ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ቱኒዚያ እና አልጄሪያ ነጥብ ተጋርተዋል
Jul 10, 2025 61
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት ጨዋታ ቱኒዚያ እና አልጄሪያ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው ማምሻውን በበፔሬ ጄጎ ስታዲየም ተካሄዷል። አልጄሪያ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድል በመፍጠር የነበራትን ብልጫ ወደ ውጤት መቀየር አልቻለችም። መርሃ ግብሩ በአፍሪካ ዋንጫው ምንም ግብ ያልተቆጠረበት የመጀመሪያው ጨዋታ ሆኗል። ውጤቱን ተከትሎ አልጄሪያ በአራት ነጥብ ምድቡን እየመራች ነው። ቱኒዚያ በአንድ ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። በምድብ ሶስት ቦትስዋና ከናይጄሪያ ምሽት 4 ሰዓት ላይ በላርቢ ዛውሊ ስታዲየም ይጫወታሉ። የዘጠኝ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋ ናይጄሪያ በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። ካሸነፈች የምድቡን መሪነት ከአልጄሪያ ትረክባለች። ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ የያዘችው ቦትስዋና የመጀመሪያ ድሏን ለማስመዝገብ ትጫወታለች።
በሴቶች አፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ
Jul 10, 2025 66
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሁለት ሁለተኛ መርሃ ግብር ዛሬ ይደረጋል። ቱኒዚያ እና አልጄሪያ ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ በፔሬ ጄጎ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቱኒዚያ በመጀመሪያ ጨዋታዋ በናይጄሪያ 3 ለ 0 ስትሸነፍ አልጄሪያ ቦትስዋናን 1 ለ 0 ረታለች። ማሸነፍ ቱኒዚያ በውድድሩ የመቆየት እድሏን እንዲሰፋ ያደርጋል። አልጄሪያ ካሸነፈች ሩብ ፍጻሜ ትገባለች። የሰሜን አፍሪካ ሀገራቱ ከዚህ ቀደም 11 ጊዜ ተገናኝተው አልጄሪያ 6 ጊዜ በማሸነፍ ብልጫውን ወስዳለች። ቱኒዚያ 2 ጊዜ ስታሸንፍ 3 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። አልጄሪያ በጨዋታዎቹ 21 ግቦችን ስታስቆጥር ቱኒዚያ 14 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፋለች። የምድብ ሁለት ሌላኛው ጨዋታ ምሽት 4 ሰዓት ላይ በላርቢ ዛውሊ ስታዲየም ናይጄሪያ እና ቦትስዋናን ያገናኛል። የዘጠኝ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋ ናይጄሪያ በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታዋ ቱኒዚያን 3 ለ 0 በመርታት ምድቡን እየመራች ነው። በአልጄሪያ የ1 ለ 0 ሽንፈት ያስተናገደችው ቦትስዋና ያለ ምንም ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። ናይጄሪያ ካሸነፈች ወደ ሩብ ፍጻሜ የሚያስገባትን ትኬት ትቆርጣለች። ቦትስዋና በምድቡ የመጀመሪያ ድሏን ለማስመዝገብ ትጫወታለች። ሁለቱ ሀገራት እ.አ.አ በ2022 ሞሮኮ ባዘጋጀችው 12ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሶስት ተገናኝተው ናይጄሪያ 2 ለ 0 ማሸነፏ የሚታወስ ነው። በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ ስድስተኛ ቀኑን ይዟል።
ፒኤስጂ ሪያል ማድሪድን በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል
Jul 10, 2025 82
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ ሁለተኛ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ፒኤስጂ ሪያል ማድሪድን 4 ለ 0 በሆነ የሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በሜትላይፍ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፋቢያን ሩዊዝ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኡስማን ዴምቤሌ እና ጎንዛሎ ራሞስ ቀሪዎቹን ጎሎች ለፈረንሳዩ ቡድን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የመጀመሪያዎቹ ሁለት ግቦች የተቆጠሩት የሪያል ማድሪድ ተከላካዮች በሰሩት ስህተት ነው። በጨዋታው ፒኤስጂ በጨዋታው በሪያል ማድሪድ ላይ ከፍተኛ ብልጫ የወሰደ ሲሆን ተጨማሪ ግቦችን ማስቆጠር ይችል ነበር። የሪያል ማድሪዱ ግብ ጠባቂ ቲቦ ኮርቶዋ ያዳናቸው ያለቀላቸው ኳሶች ቡድኑ በሰፊ ጎል እንዳይሸነፍ አድርጎታል። ሁለቱ ግቦችን ያስቆጠረው ፋቢያን ሩዊዝ የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊው ፒኤስጂ ለፍጻሜ አልፏል። በፍጻሜው ከቼልሲ ጋር ይጫወታል። የፍጻሜው ጨዋታ እሁድ ሐምሌ 6 ቀን 2017 ዓ.ም በሜትላይፍ ስታዲየም ይደረጋል። የፓሪሱ ክለብ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ዋንጫውን ለማንሳት ይፋለማል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ የክለቦቹ ባስ መንገድ ላይ በገጠመው የትራፊክ መጨናነቅ 10 ደቂቃ ዘግይቶ መጀመሩ አስገራሚ ሆኗል። ለባለንዶር ሽልማት የታጨው ኡስማን ዴምቤሌ በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ 35 ከፍ አድርጓል። ሪያል ማድሪድ ዓመቱን ያለ ዋንጫ አጠናቋል።
አዘጋጅ ሀገር ሞሮኮ የመጀመሪያ ድሏን አስመዝግባለች
Jul 10, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አንድ መርሃ ግብር ሞሮኮ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን 4 ለ 2 አሸንፋለች። ትናንት ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አምበሏ ጊዝላኔ ቼባክ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርታለች። በውድድሩ ሀትሪክ የሰራች የመጀመሪያ ተጫዋች ሆናለች። በውድድሩ ያስቆጠረቻቸውን ግቦች ወደ አራት ከፍ አድርጋለች። ያስሚን ምራቤት ለሞሮኮ ቀሪዋን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት አስቆጥራለች። ሜርቬል ናንጉጂ እና ፍላቪን ማዌቴ ለዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሞሮኮ በጨዋታው በኳስ ቁጥጥር ከፍተኛ ብልጫ የወሰደች ሲሆን የተሻለ የግብ እድልም ፈጥራለች። ውጤቱን ተከትሎ አዘጋጇ ሀገር ሞሮኮ የመጀመሪያ ድሏን አስመዝግባለች። በአራት ነጥብ ደረጃዋን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጋለች። በምድቡ ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻው አራተኛ ደረጃ ያዛለች። በዚሁ ምድብ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ዛምቢያ ሴኔጋልን 3 ለ 2 አሸንፋለች። ዛምቢያ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ሞሮኮ ከሴኔጋል የምድብ አንድ የመጨረሻ ጨዋታዎች ናቸው።
በሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ዛምቢያ ሴኔጋልን አሸነፈች
Jul 9, 2025 93
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አንድ ጨዋታ ዛምቢያ ሴኔጋልን 3 ለ 2 አሸንፋለች። ማምሻውን በኤል ባቺር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ባርባራ ባንዳ ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር ራቼል ኩንዳናንጂ ቀሪዋን ጎል ለዛምቢያ ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ንጉዌናር ንዳዬ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ሁለቱን ግቦች ለሴኔጋል አስቆጥራለች። ውጤቱን ተከትሎ ዛምቢያ ምድብ አንድን በአራት ነጥብ እየመራች ነው። ሴኔጋል በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። የሴኔጋሏ አጥቂ ንጉዌናር ንዳዬ በውድድሩ ያስቆጠረቻቸውን የግብ ብዛት ወደ አራት ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራች ነው። የዛምቢያዋ የፊት መስመር ተሰላፊ ባርባራ ባንዳ በሶስት ግቦች ትከተላለች። በዚሁ ምድብ ምሽት 4 ሰዓት ላይ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከአዘጋጇ ሞሮኮ ጋር በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሞሮኮ በአንድ ነጥብ ሶስተኛ፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ ይዛለች።
የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ
Jul 9, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ከአንድ ቀን እረፍት በኋላ በምድብ ሁለተኛ ጨዋታዎች ይመለሳል። በምድብ አንድ ሴኔጋል ከዛምቢያ ምሽት 1 ሰዓት ላይ በኤል ባቺር ስታዲየም ይጫወታሉ። ሴኔጋል በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታዋ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት በማሸነፍ ምድቡን በሶስት ነጥብ እየመራች ነው። የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፈች ሴኔጋል ለሩብ ፍጻሜ ታልፋለች። በመጀመሪያ ጨዋታዋ ከአዘጋጇ ሞሮኮ ጋር ሁለት አቻ የተለያየችው ዛምቢያ በውድድሩ ለመቆየት ማሸነፍ ግድ ይላታል። ሁለቱ ሀገራት እ.አ.አ ሞሮኮ ባሰናዳችው 12ኛው የሴቶች አፍሪካ ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ ተገናኝተው ነበር። በመደበኛ 90 ደቂቃ አንድ አቻ ተለያይተው ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቶ ዛምቢያ በመለያ ምት 4 ለ 2 አሸንፋ ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። በዚሁ ምድብ ምሽት 4 ሰዓት ላይ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከአዘጋጇ ሞሮኮ በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ዴሞክራቲክ ኮንጎ ያለ ምንም ነጥብ ሶስተኛ፣ ሞሮኮ በአንድ ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። ማሸነፍ ሀገራቱ ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባታቸውን እድል ያሰፋል። ቡድኖቹ ከዚህ ቀደም በሁለት ዓለም አቀፍ የወዳጅነት ጨዋታዎች ተገናኝተው ሞሮኮ በሁለቱም አጋጣሚ አሸንፋለች።
“ ከፍጻሜው በፊት የፍጻሜ ጨዋታ” የተባለው የፒኤስጂ እና ሪያል ማድሪድ ፍልሚያ ተጠባቂ ነው
Jul 9, 2025 83
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ ፒኤስጂ እና ሪያል ማድሪድ ዛሬ የሚያደርጉት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ የዓለም እግር ኳስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ምሽት 4 ሰዓት ላይ በሜትላይፍ ስታዲየም ይካሄዳል። ፒኤስጂ በሩብ ፍጻሜው ባየር ሙኒክን 2 ለ 0 አሸንፏል። ቡድኑ ሁለት ተጫዋች በቀይ ወጥቶበት ያስመዘገበው ውጤት አድናቆት አስችሮታል። ተጋጣሚው ሪያል ማድሪድ ቦሩሲያ ዶርትሙንድን በሩብ ፍጻሜው 3 ለ 2 በማሸነፍ አራት ውስጥ ገብቷል። ማድሪድ በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች የተቆጠሩበት ግቦች ስጋት ውስጥ ከተውት ነበር። የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊው ፒኤስጂ በሉዊስ ኤነሪኬ እየተመራ በዘንድሮው የውድድር አስደናቂ ብቃቱን እያሳየ ይገኛል። የፈረንሳይ ሊግ እና የፈረንሳይ ጥሎ ማለፍን ክብር በእጁ ያስገባው የፓሪሱ ክለብ የአውሮፓውን ቁንጮ ውድድር አሸንፏል። ድንቁን ዓመት የዓለም እግር ኳስ ትልቁን ክብር በማሸነፍ የመደምደም ህልም አለው። የ15 ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊው ሪያል ማድሪድ ያለ ዋንጫ ያጠነቀቀ ሲሆን አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ ቡድኑ ከተረከቡት በኋላ ጥሩ መሻሻል አሳይቷል። የአማካይ ክፍል የኳስ ቁጥጥር እና ፈጣን የማጥቃት ሽግግር ከክንፍ መስመር ተጫዋቾች ፈጣን እንቅሰቃሴ ጋር ተጣሮ ሎስ ብላንኮሶቹን ጥንካሬውን መልሶ እንዲያገኝ እያደረጉት ነው። ሁለቱ የአውሮፓ ኃያላን እስከ አሁን በውድድር ጨዋታዎች 13 ተገናኝተው ሪያል ማድሪድ 6 ጊዜ ሲያሸንፍ ፒኤስጂ 3 ጊዜ ድል ቀንቶል ። በሁለት ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በዛሬው ጨዋታ በሩብ ፍጻሜው ወሊያን ፓቾ እና ቲኦ ሄርናንዴዝን በቀይ ካርድ ያጣው ፒኤስጂ ተከላካዩ ላይ መጠነኛ መሳሳት ሊያጋጥመው ይችላል። ለባለንዶር የታጨው ኡስማን ኤምቤሌ ወደ ሙሉ የአካል ብቃት እና የጨዋታ ዝግጁነት መመለሱ ለፈረንሳዩ ቡድን መልካም ዜና ነው። ተጋጣሚው ሪያል ማድሪድ በሩብ ፍጻሜ ቀይ ካርድ ያየውን ዲን ሀውሰን አገልግሎት የማያገኝ ሲሆን በሱ ምትክ ራኡል አሴንሲዮ እና ኤደር ሚሊታኦ ሊሰለፉ ይችላሉ የሚሉ ግምቶች እየወጡ ነው። የኪሊያን ምባፔ ወደ መመለስ ለነጮቹ የምስራች የሆነላቸው ሲሆን አጥቂው ከዓመት በፊት በነጻ ዝውውር የለቀቀውን የቀድሞ ቡድኑን ይገጥማል። በአማካይ ክፍሉ ቪቲንሃ፣ ጆአ ኔቬስ እና ፋቢያን ሩዊዝ ከፒኤስጂ፣ ጁድ ቤሊንግሃም፣ ፌዴሪኮ ቫልቬርዶ እና አርዳ ጉለር ከሪያል ማድሪድ የሚኖራቸው ፍጥጫ የበለጠ አጓጊ ሆኗል። እጅግ ጠንካራ እና ተቀራራቢ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ በሚጠበቀው ጨዋታ ፒኤስጂ በጠበበ ሁኔታም ቢሆን ሊያሸንፍ ይችላል የሚሉ ግምቶች እየወጡ ነው። የ44 ዓመቱ ፖላንዳዊ ሲሞን ማርሲኒያክ ተጠባቂውም ፍልሚያ በመሐል ዳኝነት ይመሩታል። የሁለቱ ቡድኖች አሸናፊ በፍጻሜው ከቼልሲ ጋር ይጫወታል።
ቼልሲ ለፍጻሜ አለፈ
Jul 9, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ቼልሲ ፍሉሜኔንሴን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሜትላይፍ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በ የ60 ሚሊዮን ፓውንድ ፈራሚው ጆአኦ ፔድሮ በ18ኛው እና 56ኛው ደቂቃ ላይ በግሩም ሁኔታ ያስቆጠራቸው ግቦች ቡድኑን አሸናፊ አድርጓል። ፔድሮ የልጅነት ክለቡ ላይ ግቦቹን ካስቆጠረ በኋላ ደስታውን በተቀዛቀዘ መልኩ ገልጿል። ጨዋታው ተመጣጣኝ እና ጠንካራ ፉክክር ተደርጎበታል። ቼልሲ ለግብ የቀረቡ እድሎችን በመፍጠር የተሻለ ነበር። ጠንካራው የፍሉሜንሴ የተከላካይ መስመር በጨዋታው ላይ ባልተለመደ ሁኔታ ስህተቶችን ሲሰራ ተስተውሏል። ቡድኑ ከ11 ጨዋታዎች በኋላ ሽንፈት አስተናግዷል። የቼልሲ የአማካይ ተጫዋች ሞሰስ ካሲዬዶ በጉዳት ምክንያት በጨዋታው ማብቂያ ላይ ወጥቷል። ውጤቱን ተከትሎ ቼልሲ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ዋንጫውን ለማንሳት ከፒኤስጂ እና ሪያል ማድሪድ አሸናፊ ጋር ያደርጋል። ፒኤስጂ እና ሪያል ማድሪድ ነገ የሚያደርጉት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
በመዲናዋ ከ5 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ እና የህፃናት መጫወቻ ስፍራዎች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ
Jul 8, 2025 108
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ከ5 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ እና የህፃናት መጫወቻ ስፍራዎች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። በዛሬው ዕለት በ11 ክፍለ ከተሞች ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጎባቸው የተገነቡ 122 የስፖርት ማዘውተሪያ እና 1ሺህ 155 የህፃናት መጫወቻ ስፍራዎችን ለአገልግሎት ክፍት ተደርገዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ዛሬ ማለዳ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ መሪ ሎቄ 40/60 ኮንዶሚኒየም አካባቢና በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ እና የህፃናት መጫወቻ መሰረተ ልማቶችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ከንቲባዋ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ከተማ አስተዳደሩ በ2017 በጀት ዓመት 15ሺህ 960 ፕሮጀክቶች ገንብቶ አጠናቋል። መሰረተ ልማቶቹን ለመገንባት ከወጣው ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ 50 በመቶ የሚሆነው በከተማዋ ነዋሪዎች መሸፈኑን ነው የተናገሩት። አስተዳደሩ ባለፉት ሁለት ዓመታት ከ3ሺህ 800 በላይ የህፃናት የመጫወቻ ስፍራዎችን መገንባቱንም ገልጸዋል። ጊዜን፣ እውቀትንና የማህበረሰቡን ተሳትፎ በማቀናጀት ለህፃናት እና ለወጣቶች ቅድሚያ በመስጠት እየተሰራ መሆኑን አክለዋል። ስራዎቹ ህፃናትና ወጣቶች በአካልና በአዕምሮ ብቁ ሆነው እንዲያድጉ የሚያስችሉ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በቀጣይ በስፖርቱ ዘርፍ በዓለምና በአህጉር መድረክ የተሻለ ውጤት ለማምጣት አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱም ጠቅሰዋል። የከተማ አስተዳደሩ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ በላይ ደጀን በበኩላቸው፤ በከተማዋ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች በአዕምሮና በአካል የዳበረ ሀገር ተረካቢ ትውልድ ለመገንባት ተቀሜታቸው የጎላ ነው ብለዋል።
ፍሉሜኔንሴ እና ቼልሲ ለክለቦች የዓለም ዋንጫ ፍጻሜ ለማለፍ ይፋለማሉ
Jul 8, 2025 82
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ፍሉሜኔንሴ እና ቼልሲ ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ላይ በሜትላይፍ ስታዲየም ይካሄዳል። የብራዚሉ ፍሉሜኔንሴ በሩብ ፍጻሜው የሳዕዲ አረቢያውን አል ሂላልን 2 ለ 1 አሸንፏል። የእንግሊዙ ቼልሲ የብራዚሉን ፓልሜራስ 2 ለ 1 በመርታት የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብቷል። ባለፉት 11 ጨዋታዎችን ሽንፈትን ያላየው ፍሉሜኔንሴ በዓለም ዋንጫው ግምቶችን ፉርሽ በማድረግ ግማሽ ፍጻሜ ደርሷል። ጠንካራ የተከላካይ ክፍል መስመሩ እና የመልሶ ማጥቃት የአጨዋወት ስልቱ ለተጋጣሚው ራስ ምታት ሆኗል። በሬናቶ ጋውቼ የሚመራው ፍሉሚኔንሴ በባለፈው የውድድር ዓመት በብራዚል ሴሪ አ ከመውረድ ተርፎ በአጭር ጊዜ እያሳየ ያለው አስገራሚ ብቃት አሰልጣኙን አስወድሷቸዋል። የኢንዞ ማሬስካው ቼልሲ በፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ በአማካይ ተጫዋቹ የፈጠራ አቅም፣ የታክቲክ ተለዋዋጭነት እና የኳስ የመቆጣጠር አቅም ታግዞ ጥሩ ግስጋሴ እያደረገ ይገኛል። ይሁንና የተከላካይ ክፍል መስመሩ ተጋላጭነት ተጋጣሚዎቹ ግብ እንዲያስቆጥርበት ሲያደርጉ ለመመልከት ተችሏል። ሁለቱ ቡድኖች እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። የእግር ኳስ ልሂቃኑ እና ተመልካቹ ለቼልሲ የማሸነፍ እድሉን በስፋት ቢሰጡም ተጋጣሚው ፍሉሜኔንሴ ያልተጠበቀ ድል ሊያስመዘግብበት እድል አለ የሚሉ አልጠፉም። ቼልሲ ጨዋታውን ለማሸነፍ ጠንካራውን የብራዚል ክለብ የመከላከል ግድግዳ ማፍረስ ይጠበቅበታል። ፍሉሜኔንሴ ጠንካራ የመከላከል ቅርጹን ጠብቆ በሚያገኛቸው አጋጣሚዎች በመልሶ ማጥቃት ግቦችን ለማስቆጠር የሚያስችል የጨዋታ ስልት ወደ ሜዳ ይዞ ይገባል ተብሎ ይጠበቃል። የፍሉሜንሴው ብራዚላዊ የ40 ዓመት አምበል ቲያጎ ሲልቫ የቀድሞ ክለቡን ቼልሲን የሚገጥምበት ጨዋታ መሆኑንም ትኩረት ስቧል። የ36 ዓመቱ ፈረተንሳዊ ፍራንስዊ ሌቲክሲየር ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። የሁለቱ ቡድኖች አሸናፊ በፍጻሜው ከፒኤስጂ ወይም ከሪያል ማድሪድ አሸናፊ ጋር ይገናኛል። በአሜሪካ አስተጋጅነት እየተካሄደ ያለው የፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ ዛሬ 22ኛ ቀኑን ይዟል።
በሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ማሊ ታንዛንያን አሸነፈች
Jul 8, 2025 85
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት ጨዋታ ማሊ ታንዛንያን 1 ለ 0 አሸንፋለች ። ማምሻውን በቤርካኔ ሙኒሲፓል ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አጥቂዋ ሳራቱ ትራኦሬ በመጀመሪያ አጋማሽ ጭማሪ ደቂቃዎች ላይ የማሸነፊያዋን ጎል አስቆጥራለች። ማሊ በጨዋታው ብልጫ ቢወሰድባትም ያስቆጠረችውን ብቸኛ ግብ አስጠብቃ ወጥታለች። ታንዛንያ በጨዋታው ላይ የነበራትን የተሻለ የኳስ ቁጥጥር እና ኢላማቸውን የጠበቁ ሙከራዎች ወደ ግብ መቀየር አልቻለችም። ውጤቱን ተከትሎ ማሊ በምድብ ሶስት በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ምድብ ዛሬ በተካሄደው የመጀመሪያ ጨዋታ የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ ባለቤት ደቡብ አፍሪካ ጋናን 2 ለ 0 አሸንፋለች። የምድቡ መሪም ሆናለች። ጋና ከማሊ፣ ታንዛንያ ከደቡብ አፍሪካ በምድቡ የሚደረጉ ቀጣይ ጨዋታዎች ናቸው።
ደቡብ አፍሪካ የአፍሪካ ዋንጫ ክብር የማስጠበቅ ጉዞዋን በድል ጀምራለች
Jul 7, 2025 108
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2017 (ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት የመጀመሪያ መርሃ ግብር ደቡብ አፍሪካ ጋናን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሆነር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሊንዳ ሞትልሃሎ በፍጹም ቅጣት ምት እና ጀርሜን ሲኦፖሴንዌ በጨዋታ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር የተደረገበት ሲሆን ደቡብ አፍሪካ ያገኘችውን የግብ እድል በሚገባ መጠቀሟ ባለድል አድርጓታል። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ደቡብ አፍሪካ ጉዞዋን በድል ጀምራለች። ምድቧንም በሶስት ነጥብ እየመራች ነው። ጋና ያለ ምንም ነጥብ በምድቡ የመጨረሻ ደረጃ ላይ ትገኛለች።
የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የሶስተኛ ቀን ውሎ
Jul 7, 2025 97
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2017(ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት የመጀመሪያ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ በሆነር ስታዲየም ደቡብ አፍሪካ ከጋና ይጫወታሉ። ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ2022 በሞሮኮ በተካሄደው 12ኛው የሴቶች አፍሪካ ዋንጫ በፍጻሜው አዘጋጇን ሀገር 2 ለ 1 በመርታት ዋንጫ ማንሳቷ የሚታወስ ነው። በተጨማሪም በውድደሩ ተሳትፏቸው ታሪክ አራት ጊዜ ሁለተኛ፣ ሁለት ጊዜ ሶስተኛ እና ሶስት ጊዜ አራተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ተጋጣሚዋ ጋና በአፍሪካ ዋንጫ ሶስት ጊዜ ለፍጻሜ ደርሳ በሶስቱም ተሸንፋለች። በውድድሩ ሶስት ጊዜ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ ከዋንጫ መለስ ጠንካራ ተሳትፎ አድርጋለች። ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም 11 ጊዜ እርስ በእርስ ተገናኝተዋል። ደቡብ አፍሪካ በአራቱ ድል ሲቀናት ጋና ሶስት ጊዜ አሸንፋለች። አራት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥተዋል። ጋና በጨዋታዎቹ 11 ግቦችን ስታስቆጥር ደቡብ አፍሪካ 10 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፋለች። በፊፋ የሴቶች የሀገራት እግር ኳስ ደረጃ ደቡብ አፍሪካ 54ኛ፣ ጋና 66ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። በዚሁ ምድብ ምሽት 4 ሰዓት ላይ ማሊ ከታንዛንያ በቤርካኔ ሙኒሲፓል ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም ሁለት ጊዜ ተገናኝተው ማሊ አንድ ጊዜ ስታሸንፍ በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። እ.አ.አ ሜይ 31 2024 በዳሬሰላም ባደረጉት ዓለም አቀፍ የወዳጅነት ጨዋታ ሁለት አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በፊፋ የሴቶች የሀገራት እግር ኳስ ደረጃ ማሊ 78ኛ፣ ታንዛንያ 137ኛ ደረጃን ይዘዋል።
አልጄሪያ ድል ቀንቷታል
Jul 7, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29 /2017 (ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ አልጄሪያ ቦትስዋናን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ትናንት ማምሻውን በፔሬ ጄጎ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአማካይ ተጨዋቿ ጉቲያ ካርቹኒ በ10ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ግቧን አስቆጥራለች። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል ። ውጤቱን ተከትሎ አልጄሪያ በምድብ ሁለት በሶሰት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ምድብ ትናንት በተካሄደ የመጀመሪያ ጨዋታ ናይጄሪያ ቱኒዚያ 3 ለ 0 አሸንፋለች። ናይጄሪያ ከቦትስዋና፣ ቱኒዚያ ከአልጄሪያ በቀጣይ በምድቡ የሚደረጉ ተጫዋቾች ናቸው።
የአፍሪካ ዋንጫ ባለብዙ ክብሯ ናይጄሪያ ጉዟዋን በድል ጀምራለች
Jul 7, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2017 (ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሁለት የመጀመሪያ ጨዋታ ናይጄሪያ ቱኒዚያን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ትናንት ማምሻውን በላርቢ ዛውሊ ስታዲየም በተካሄደው አሲሳት ኦሾላ፣ ባባጂንዴ ሪንሶላ እና ቺንዌንዱ ልሄዙ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አጥቂዋ ባባጂንዴ ሪንሶላ ግቡን ካስቆጠረች በኋላ በቅርብ በመኪና ህይወቱ ያለፈውን ዲያጎ ጆታ የደስታ አገላለጽ በመጠቀም ተጫዋቹን አስታውሳለች። የዘጠኝ ጊዜ የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫን በማንሳት የበላይ የሆነችው ናይጄሪያ ምድብ ሁለትን መምራት ጀምራለች። ቱኒዚያ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃን ይዛለች።
ሴኔጋል ድል ቀንቷታል
Jul 6, 2025 112
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29 /2017 (ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አንድ ሁለተኛ መርሃ ግብር ሴኔጋል ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፋለች። በኤል ባቺር ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ማማ ዲዮፕ እና ንጌናር ንዳዬ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን አስቆጥረዋል። በጨዋታው ሴኔጋል በዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ላይ ከፍተኛ ብልጫ ወስዳለች። ውጤቱን ተከትሎ ሴኔጋል ምድብ አንድን በሶስት ነጥብ መምራት ጀምራለች። በዚሁ ምድብ ትናንት በተካሄደ የመጀመሪያ ጨዋታ አዘጋጇ ሞሮኮ ከዛምቢያ ሁለት አቻ ተለያይታለች።
በሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ
Jul 6, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29/2017(ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። በምድብ አንድ ሴኔጋል ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በኤል ባቺር ስታዲየም ይጫወታሉ። ሁለቱ ቡድኖች ከዚህ ቀደም እርስ በእርስ ባደረጓቸው ሶስት ጨዋታዎች ዶሜክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ሁለት ጊዜ ስታሸንፍ ቀሪውን ጨዋታ ሴኔጋል አሸንፋለች። በፊፋ የሴቶች የሀገራት እግር ኳስ ደረጃ ሴኔጋል 81ኛ፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ 109ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። በዚሁ ምድብ ትናንት በተደረገው የመክፈቻ ጨዋታ ሞሮኮ እና ዛምቢያ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። የአፍሪካ ዋንጫን ዘጠኝ ጊዜ በማንሳት የውድድሩ ቁንጮ ሀገር የሆነችው ናይጄሪያ ከቱኒዚያ ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ በላርቢ ዛውሊ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ሁለቱ የአፍሪካ ሴቶች እግር ኳስ ተቀናቃኝ ሀገራት እስከ አሁን ዘጠኝ ጊዜ እርስ በእርስ ተገናኝተዋል። ናይጄሪያ ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ ቱኒዚያ ሁለት ጊዜ አሸንፋለች። አራት ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በዘጠኙ ጨዋታዎች ናይጄሪያ 11 ግቦችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ፣ ቱኒዚያ 9 ጎሎችን አስቆጥራለች። በሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ከፍተኛ የበላይነት ያላት ናይጄሪያ ጨዋታውን የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት አግኝታለች። በፊፋ የሴቶች የሀገራት እግር ኳስ ደረጃ ናይጄሪያ 36ኛ፣ ቱኒዚያ 89ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። በዚሁ ምድብ ምሽት 4 ሰዓት ላይ አልጄሪያ ከቦትስዋና በፔሬ ጄጎ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሁለቱ ሀገራት በውድድር ጨዋታዎች ሲገናኙ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ያደረጓቸውን ሶስት ጨዋታዎች አልጄሪያ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዛለች። አልጄሪያ በጨዋታዎቹ 10 ግቦችን ስታስቆጥር ቦትስዋን ማግባት የቻለቸው አንድ ጎል ብቻ ነው። ጨዋታው አልጄሪያ በቦትስዋና ላይ ያላትን የበላይነት ለማስቀጠል፣ ቦትስዋን በተጋጣሚዋ ላይ የመጀመሪያ ድሏን ለማስመዝገብ የሚያደርጉት ጨዋታ ነው። በፊፋ የሴቶች የሀገራት እግር ኳስ ደረጃ አልጄሪያ 82ኛ፣ ቦትስዋና 153ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ።
ሪያል ማድሪድ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል
Jul 6, 2025 84
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ ሪያል ማድሪድ ቦሩሲያ ዶርትሙንድን 3 ለ 2 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በሜትላይፍ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ጎንዛሎ ጋርሺያ፣ ፍራንሲስኮ ጋርሺያ እና ኪሊያን እምባፔ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ማክሲሚሊያን ቤየር በጨዋታ እና ሴርሁ ጉይራሲ በፍጹም ቅጣት ምት ለቦሩሲያ ዶርትሙንድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የሪያል ማድሪድ ተከላካይ ዲን ሀውሰን በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። በጨዋታው ሪያል ማድሪድ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድሎችን በመፍጠር ከተጋጣሚው የተሻለ ነበር። ውጤቱን ተከትሎ ሪያል ማድሪድ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። ለፍጻሜ ለማለፍ ከፒኤስጂ ጋር የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ወጣቱ አጥቂ ጎንዛሎ ጋርሺያ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ አራት ከፍ አድርጓል። ጋርሺያ ከውድድሩ ከተሰናበቱት የአል ሂላሉ ማርኮስ ሌኦናርዶ እና የቤኔፊካው አንጌል ዲ ማሪያ ጋር በግብ ተስተካክሏል። ታዳጊው አጥቂ ተጨማሪ ግቦችን አስቆጥሮ ኮከብ ግብ አግቢ የመሆን እድል አለው። ትናንት በተደረገው ሌላኛው የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ ፒኤስጂ ባየር ሙኒክን 2 ለ 0 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ በፍሉሜኔንሴ እና ቼልሲ መካከል ይደረጋል። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ሐምሌ 1 እና 2 ቀን 2017 ዓ.ም ይካሄዳሉ።
በሴቶች አፍሪካ ዋንጫ መክፈቻ ሞርሮኮ እና ዛምቢያ አቻ ተለያዩ
Jul 6, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29/2017(ኢዜአ)፦ በ13ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የመክፈቻ ጨዋታ አዘጋጇ ሞሮኮ ከዛምቢያ ሁለት አቻ ተለያይታለች። ትናንት ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም በተካሄደው የምድብ አንድ ጨዋታ ኢብቲሳም ጂራይዲ እና ጊዝላን ቼባክ ግቦቹን ለሞሮኮ አስቆጥረዋል። ባርባራ ባንዳ እና ራቼል ኩንዳንናንጂ ለዛምቢያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ሁለቱ ሀገራት ተመጣጣኝ ፉክክር አድርገዋል። ውጤቱን ተከትሎ በምድብ አንድ ሞሮኮ እና ዛምቢያ በምድቡ የመጀመሪያ ነጥባቸውን አግኝተዋል። በዚሁ ምድብ ሴኔጋል ከዴሞክራቲክ ኮንጎ ዛሬ ከቀኑ 11 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ከጨዋታው በፊት ደማቅ የመክፈቻ ስነ ስርዓት ተካሂዷል። እስከ ሐምሌ 19 ቀን 2017 ዓ.ም በሚቆየው ውድድር 12 ሀገራት በሶስት ምድብ ተከፍለው ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ድራማዊ ክስተቶችን ባስተናገደው አስገራሚ ጨዋታ ፒኤስጂ ባየር ሙኒክን በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል
Jul 5, 2025 110
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 28/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ ተጠባቂ መርሃ ግብር ፒኤስጂ ባየር ሙኒክን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሜርሴዲስ-ቤንዝ ስታዲየም ዴዚሬ ዱዌ በ78ኛው እና ኡስማን ዴምቤሌ በ96ኛው ደቂቃ የማሸነፊያዋን ጎል አስቆጥረዋል። ጠንካራ ፉክክር በተደረገበት የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ለግብ የቀረቡ በርካታ እድሎች ፈጥረዋል። የፒኤስጂው ግብ ጠባቂ ጂያንሉዊጂ ዶናሩማ እና የባየር ሙኒክ ግብ ጠባቂ ማኑኤል ኖየር ግብ የሚሆኑ ኳሶችን በአስደናቂ ሁኔታ አድነዋል። የፒኤስጂ ተከላካዮች ዊሊያን ፓቾ እና ሉካስ ሄርናንዴዝ በፈጸመው ጥፋት በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብተዋል። በጨዋታው ባየር ሙኒክ ሁለት ግቦችን አስቆጥረው ከጨዋታ ውጪ በመሆናቸው ተሽረዋል። በጨዋታው ማጠናቀቂያ ላይ ፍጹም ቅጣት ምት አግኝቶም በቪዲዮ የታገዘ ዳኝነት (ቫር) ተሽሯል። በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ ማብቂያ የባየርሙኒኩ የክንፍ ተጫዋች ጀማል ሙሲያላ ከፒኤስጂ ግብ ጂያንሉዊጂ ዶናሩማ ጋር በመጋጨቱ ምክንያት በግራ እግሩ ቁርጭምጭሚት ከፍተኛ ጉዳት አስተናግዶ ተቀይሮ ወጥቷል። የተጫዋቹ አሰቃቂ ጉዳት በሁለቱ ቡድኖች ተጫዋቾች ከፍተኛ ድንጋጤ እና ፍርሃት ፈጥሮ ነበር። ሙሲያላ ወደ ሆስፒታል በማምራት ህክምናውን እየተከታተለ ይገኛል። ጉዳቱ ተጫዋቹን ለረጅም ጊዜ ከሜዳ ሊያርቀው ይችላል። ለ102 ደቂቃዎች የቆየው ጨዋታ አዝናኝ፣ ልብ አንጠልጣይ እና በክስተቶች የተሞላ ነበር። ውጤቱን ተከትሎ የአውሮፓ ሻምፒዮኑ ፒኤስጂ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። ቡድኑ ከሪያል ማድሪድ እና ቦሩሲያ ዶርትሙንድ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። የመጨረሻው የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ በሪያል ማድሪድ እና ቦሩሲያ ዶርትሙንድ መካከል ምሽት 5 ሰዓት ላይ በሜትላይፍ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።