ስፖርት
የጣልያን ሴሪ አ ዋንጫን ማን ያነሳል? ናፖሊ ወይስ ኢንተር ሚላን? 
May 23, 2025 42
አዲስ አበባ ፤ ግንቦት 15/2017(ኢዜአ)፡- የ2024/25 የጣልያን ሴሪ አ ዋንጫን አሸናፊ የሚለዩ ሁለት ወሳኝ ጨዋታዎች ዛሬ ማምሻውን ይደረጋሉ። በመጨረሻው የ38ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ናፖሊ ከካግሊያሪ በሜዳው፣ ኢንተር ሚላን ከኮሞ ከሜዳው ውጪ ከኮሞ ጋር በተመሳሳይ ምሽት 3 ሰዓት ከ45 ላይ ይጫወታሉ። ናፖሊ በ79 ነጥብ ሊጉ እየመራ ነው። ኢንተር ሚላን በ78 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። የውድድር ዓመቱን ተመጣጣኝ እና ተቀራረቢ ፉክክር ያደረጉት ቡድኖቹ የዋንጫው አሸናፊ ለመሆን የመጨረሻውን ሳምንት መጠበቅ ግድ ብሏቸዋል። ናፖሊ በሊጉ ባደረጋቸው 37 ጨዋታዎች 23 ጊዜ ሲያሸንፍ 4 ጊዜ ተሸንፏል። 10 ጊዜ አቻ ወጥቷል። 57 ጎሎችን ሲያስቆጥር 27 ጎሎችን አስተናግዷል። ተከታዩ ኢንተር ሚላን በሊጉ እስከ አሁን ባካሄዳቸው 37 ጨዋታዎች 23 ጊዜ ድል ሲቀናው 5 ጊዜ ተሸንፏል። 9 ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ቡድኑ 77 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 35 ግቦች ተቆጥረውበታል። ናፖሊ ካግሊያሪን ካሸነፈ የኢንተር ሚላንን ውጤት ሳይጠብቅ ዋንጫውን ያነሳል። በአንጻሩ የአምናው የሊጉ አሸናፊ ዋንጫውን ለማንሳት ኮሞን አሸንፎ ናፖሊ ነጥብ መጣል ይኖርበታል። ናፖሊ ተሸንፎ ኢንተር ሚላን አቻ ቢወጣ ሁለቱ ቡድኖች ተመሳሳይ 79 ነጥብ ይኖራቸዋል። ቡድኖቹ በዘንድሮው የውድድር ዓመት በነበራቸው ሁለት የእርስ በእርስ ግንኙነቶች በተመሳሳይ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በሊጉ አወዳዳሪ አካል ደንብ መሰረት ሁለት ቡድኖች ተመሳሳይ ነጥብ እና በእርስ በእርስ ግንኙነታቸው እኩል ውጤት ካስመዘገቡ የዋንጫውን አሸናፊ የሚለይ የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ይደረጋል። በዛሬ ምሽት መርሃ ግብር ይህ አጋጣሚ የሚፈጠር ከሆነ አሸናፊ ለመለየት ሁለቱ ቡድኖች የፊታችን ሰኞ ግንቦት 18 ቀን 2017 ይጫወታሉ። ከዚህ ቀደም የጣልያን ሴሪ አ ዋንጫን አሸናፊ በጥሎ ማለፍ ሕግ የተለየው በአንድ አጋጣሚ ብቻ ነው። እ.አ.አ በ1963/64 የውድድር ዓመት ቦሎኛ እና ኢንተር ሚላን በተመሳሳይ 54 ነጥብ እና እኩል የእርስ የእርስ በእርስ ግንኙነት ውጤት በማጠናቀቃቸው ወደ መለያ ጨዋታ አምርተዋል። ቦሎኛ ኢንተር ሚላንን 2 ለ 0 በማሸነፍ የስኩዴቶውን ዋንጫ ከፍ አድርጓል። ከ61 ዓመት በኋላ ተመሳሳይ ታሪክ ሊደገምበት የሚችልበት እድል አለ። ናፖሊ ከዚህ ቀደም የሴሪ አ ዋንጫን ሶስት ጊዜ አንስቷል። ኢንተር ሚላን 20 ጊዜ የዋንጫው ባለቤት ሆኗል። የጣልያን ሴሪ አ ዋንጫ ወዴት ያመራል ወደ ኔፕልስ ወይስ ወደ ዋና ከተማዋ ሚላን? የሚለው ጉዳይ የዓለም እግር ኳስ አፍቃሪያን መነጋገሪያ ሆኗል።
የዋንጫ ተፎካካሪዎቹ  ኢትዮጵያ መድን እና ኢትዮጵያ ቡና የሚያደርጉት ተጠባቂ ጨዋታ 
May 23, 2025 38
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2017 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 31ኛ ሳምንት የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን እና ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ኢትዮጵያ ቡና ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ የእግር ኳስ ተመልካቹን ትኩረት ስቧል። የ31ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጀመራል። በዕለቱ ከሚደረጉት ጨዋታዎች መካከል ኢትዮጵያ መድን እና ኢትዮጵያ ቡና ከምሽቱ 12 የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ኢትዮጵያ መድን በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 28 ጨዋታዎች 18 ጊዜ ሲያሸንፍ 4 ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። 6 ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። 38 ግቦችን ሲያስቆጥር 12 ግቦችን አስተናግዷል። በአሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ የሚመራው መድን በ60 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና በሊጉ ባካሄዳቸው 28 ጨዋታዎች 15 ጊዜ ሲያሸንፍ 7 ጊዜ ተሸንፏል። 6 ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ 26 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 14 ግቦችን አስተናግዷል። በነጻነት ክብሬ የሚሰለጥነው ኢትዮጵያ ቡና በ51 ነጥብ 2ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኖቹ የሚያደርጉት ጨዋታ በዋንጫ ፉክክሩ ትልቅ ትርጉም የሚሰጠው መርሃ ግብር ነው። በሌላኛው የ31ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አስቀድሞ ከሊጉ መውረዱ የተረጋገጠው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ14 ነጥብ የመጨረሻውን 18ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ35 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የ31ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ግንቦት 18 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስፖርታዊ ውድድር ተጠናቀቀ
May 22, 2025 66
አሶሳ፤ግንቦት 14/2017(ኢዜአ):-በባምባሲ ከተማ ለ12 ተከታታይ ቀናት የተካሄደው 6ኛው መላው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስፖርታዊ ጨዋታዎች ውድድር ተጠናቀቀ። በውድድሩ 16 ወረዳዎች በ11 የስፖርት ዓይነቶች የተሳተፉ ሲሆን አሶሳ ከተማ አስተዳደር ወረዳ አንድ አጠቃላይ አሸናፊ ሆኗል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ኢብራሂም መንሱር፥ ውድድሩ ክልሉ በሁሉም ስፖርት አይነቶች አቅም እንዳለው ያሳየበት ነው ብለዋል። በቀጣይም ለስፖርት ልማት ትኩረት በመስጠት ክልሉ ተተኪ ስፖርተኞችን እንዲያፈራ ይሰራል ብለዋል። በውድድሩ ክልሉን በሀገር አቀፍ ውድድር የሚወክሉ 128 ስፖርተኞች መመረጣቸውን ገልጸዋል። በውድድሩ በአትሌቲክስ ስፖርት የተሳተፈችው ደራርቱ መልካሙ ውድድሩ አቅማችን የፈተሽንበት እና በርካታ ተፎካካሪዎች ያየንበት ነው ብላለች። ሌላው በፓራ ኦሎምፒክ የተሳተፈው መልሰው ለሜሳ፥ ውድድሩ የአካል ጉዳተኞችን በማካተቱ ደስተኛ መሆኑን ተናግሮ፥ ስፖርት ሁሉንም አካታች መሆን እንዳለበት አመልክቷል። ውድድሩ በክልሉ ተዘውታሪ ያልሆኑ የስፖርት አይነቶች እንዲታዩ ዕድል ፈጥሯል ያለው ደግሞ ሌላው የውድድሩ ተሳታፊ አብዱሰላም አብድ ነው። የባምባሲ ከተማ ስፖርተኞችን ተቀብሎ በማስተናገድ ያደረገው ዝግጅት የሚደነቅ መሆኑን ገልጿል። በተለያዩ የስፖርት አይነቶች አሸናፊ ለሆኑ ተወዳዳሪዎች የዋንጫ እና የሜዳልያ ሽልማት ተሰጥቷል። በዕለቱም የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክትል አፈጉባኤ አቶ መለሰ ኪዊ፣ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አቶ አስር ኢብራሂም፣የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እና የስፖርት ቤተሰቦች ተገኝተዋል።
ክሮሺያዊው የመሐል ሜዳ ሞተር ሉካ ሞድሪች ከ13 ዓመታት ቆይታ በኋላ ሪያል ማድሪድን ሊለቅ ነው
May 22, 2025 54
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14 /2017 (ኢዜአ)፡- የ39 ዓመቱ አንጋፋ ተጫዋች ሉካ ሞድሪች በክረምት ወር ከሚደረገው የዓለም ክለቦች ዓለም ዋንጫ በኋላ ሪያል ማድሪድን እንደሚለቅ አስታወቀ። ሞድሪች በሳንቲያጎ በርናባው ስታዲየም የመጨረሻ ጨዋታውን የፊታችን ቅዳሜ ቡድኑ ሪያል ሶሲዬዳድን በሚያስተናግድበት የስፔን ላሊጋ የመጨረሻ ሳምንት መርሃ ግብር እንደሚያደርግ ስካይ ስፖርትስ ዘግቧል። ክሮሺያዊው ኮከብ በኢንስታግራም ገጹ ባሰፈረው መልዕክት እንዲመጣ የማልፈልገው ጊዜ መጥቷል፣ ይህ እግር ኳስ ነው ሲል ገልጿል። በህይወት ሁሉም ነገር መጀመሪያ እና መጨረሻ አለው ሲል ተናግሯል። ቅዳሜ በበርናባው የመጨረሻ ጨዋታውን እንደሚያደርግ ጠቁሟል። ለሪያል ማድሪድ መጫወቴ እንደ እግር ኳስ እና እንደ ግለሰብ ቀይሮኛል ያለው ሞድሪች በክለቡ ስኬታማ እና ወርቃማ ጊዜ ተብሎ ከሚጠቀሱ ዘመኖች መካከል የአንዱ አካል በመሆኔ ኩራት ይሰማኛል ብሏል። የሪያል ማድሪድ ክለብን ከልቤ ማመስገን እፈልጋለሁ በተለይም ፕሬዝዳንት ፍሎረንቲኖ ፔሬዝ፣ የቡድን አጋሮቼ፣ አሰልጣኞች እና ደጋፊዎችን አመስግኗል። በአሜሪካ ከሚካሄደው ከፊፋ የዓለም ክለቦች ዋንጫ በኋላ በሜዳ ውስጥ የሪያል ማድሪድን ማልያ ባለብስም፤ ሁሌም የማድሪድ ደጋፊ ሆኜ እቀጥላለሁ ሲል ተናግሯል። የሪያል ማድሪድ ፕሬዝዳንት ፍሎረንቲኖ ፔሬዝ ሁሌም በሪያል ማድሪድ ደጋፊዎች ልብ ውስጥ ይኖራል፤ በክለቡ ያሳረፈው አሻራ ሁሉም ህያው ሆኖ ይቀጥላል ሲሉ አድናቆታቸውን ገልጸውለታል። እ.አ.አ በ2012 ከቶተንሃም ሆትስፐርስ ወደ ሪያል ማድሪድ ያቀናው ሉካ ሞድሪች በሎስ ብላንኮሶቹ በነበረው ቆይታ 6 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፣ 4 የላሊጋ እና 2 የኮፓ ዴላሬይን ጨምሮ በአጠቃላይ 28 ዋንጫዎችን አንስቷል። በክለቡ ታሪክ በርካታ ዋንጫ ያነሳ ተጫዋችም ነው።
በመላው አማራ ስፖርታዊ ውድድር ኮምቦልቻ ከተማ አጠቃላይ አሸናፊ ሆነ
May 22, 2025 54
ደሴ፤ግንቦት 14/2017( ኢዜአ)፦በደሴ ከተማ ለተከታታይ 12 ቀናት በተካሄደው የመላው አማራ ስፖርታዊ ውድድር ኮምቦልቻ ከተማ አጠቃላይ አሸናፊ ሆነ። ሰሜን ሸዋና ደቡብ ወሎ ዞኖች ሁለተኛና ሶስተኛ በመሆን ውድድራቸውን አጠናቀዋል። ውድድሩ በእግርና መረብ ኳስ፣ አትሌቲክስ ጨምሮ በ19 የስፖርት አይነቶች ተካሂዷል። የአማራ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ እርዚቂ ኢሳ በማጠናቀቂያ ስነ ስርአቱ ላይ እንደገለፁት፥ ውድድሩ በክልሉ የተቀዛቀዘውን ስፖርት በማነቃቃት ጤናማና አምራች ዜጋ ለመፍጠር የሚያስችል ነው። የተጀረውን መነቃቃት በማስቀጠል ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን በማስፋፋትና በማልማት ላይ በማተኮር ይሰራል ብለዋል። በውድድሩ ከ5 ሺህ በላይ ስፖርተኞች መሳተፋቸውን ጠቁመው የእርስ በእርስ ግንኙነትን በማጠናከር ስለሰላም መስበክ ተችሏል ብለዋል። ለመላው ኢትዮጵያ ጨዋታ ክልሉን የሚወክሉ ስፖርቶችን መምረጥ መቻሉን ጠቁመው፥ ጨዋታው በስኬት እንዲጠናቀቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ሁሉ ምስጋና አቅርበዋል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሞላልኝ በበኩላቸው፥ ውድድሩ የከተማውን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴ ማነቃቃቱን ጠቁመዋል። በስፖርታዊ ውድድሮች አንድነትን፣ሰላምንና ልማትን ለማጠናከር የሚደረገው ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። በውድድሩ ኮምቦልቻ ከተማ በ47 ወርቅ፣ በ29 ብርና በ25 ነሀስ 1ኛ በመሆን አጠቃላይ አሸናፊ ሆኗል። ሰሜን ሸዋ ዞን በ30 ወርቅ፣በ20 ብርና በ18 ነሀስ 2ኛ እንዲሁም ደቡብ ወሎ ዞን በ30 ወርቅ፣ በ19 ብርና በ25 ነሀስ 3ኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል። ዛሬ በተካሄደው የማጠቃለያ የእግር ኳስ የፍጻሜ ጨዋታ ሰሜን ወሎ ዞን የእግር ኳስ ቡድን የደሴ ከተማ አቻውን በማሸነፍ ዋንጫ አንስቷል።
የማንችስተር ዩናይትድ እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ ተጠባቂ የዩሮፓ ሊግጨዋታ 
May 21, 2025 114
አዲስ አበባ ፤ ግንቦት 13/2017(ኢዜአ)፡- በ2025 የዩሮፓ ሊግ ፍጻሜ ማንችስተር ዩናይትድ እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ ዛሬ የሚያደርጉት ፍልሚያ ሁሉም አይኖች አርፈውበታል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ 53 ሺህ ተመልካች በሚያስተናገደው በስፔን ባስክ በሚገኘው ሳን ማሜስ ስታዲየም ይካሄዳል። ሁለቱ የእንግሊዝ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ በታሪካቸው መጥፎ የሚባል የውድድር ጊዜ ባሳለፉበት “ከክፉ የታሪክ ጠባሳ መዳኛ” ያሉትን ዋንጫ ለማንሳት ይፋለማሉ። ማንችስተር ዩናይትድ በሊጉ 39 ነጥብ በመያዝ 16ኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ 21 ሽንፈት አስተናግዷል። የለንደኑ ክለብ ቶተንሃም ሆትስፐርስ በሊጉ እስከ አሁን 18 ሽንፈትን አስተናግዶ በ38 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባሳዩት የወረደ ብቃት የሰላ ትችት ያስተናገዱት ሁለቱ ክለቦች የአውሮፓው መድረክ ብቸኛው ጥሩ ነገራቸው ነው ማለት ይቻላል። ማንችስተር ዩናይትድ በዩሮፓ ሊግ ግማሽ ፍጻሜ የፍጻሜ ጨዋታውን የሚያስተናግደው ስታዲየም ባለቤት አትሌቲኮ ቢልባኦን በድምር ውጤት 7 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። ዩናይትድ በዘንድሮው ዩሮፓ ሊግ ብቸኛው ያልተሸነፈ (በ12 ጨዋታዎች) ክለብ ነው። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በበኩሉ በኖርዌይ ትንሿ ከተማ ቦዶ የሚገኘውን ቦዶ ግሊምትን በደርሶ መልስ 5 ለ 1 በማሸነፍ የፍጻሜ ተፋላሚ ሆኗል። ቡድኖች መጥፎ ዓመታቸውን በዋንጫ እና በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ለማጠናቀቅ የዛሬው ጨዋታ እጅግ በጣም ወሳኝ ነው። የማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሩበን አሞሪም የዩሮፓ ሊግ ዋንጫን ማንሳት ለእኔ ትንሹ ችግር ነው፤ ክለቡ ከዛ የጠለቀ ፈተናዎች አሉበት ሲል ተናግሯል። ዋንጫውን ማንሳት ለደጋፊዎቻችን የምናደርገው ትንሹ ነገር ነው ብሏል። የቶተንሃም ሆትስፐርሱ አሰልጣኝ አንጌ ፖስቶኮግሉ ዋንጫውን ብናነሳ የዚህ ዓመት መጥፎ የውድድር ዓመታችንን ዞር ብሎ የሚያስታውሰው የለም ነው ያሉት። ዋንጫው ከክለቡ ቀጣይ ጉዞ ወሳኝ የሚባል ነው ሲልም ገልጿል። ጉዳት ላይ የነበረው የማንችስተር ዩናይትድ አጥቂ ጆሹዋ ዚርክዜ ሙሉ ለሙሉ አገግሞ ወደ ቢልባኦ መጓዙ ለማንችስተር ዩናይትድ መልካም ዜና ሆኗል። ዴጃን ኩሉሴቭስኪ፣ ጀምስ ማዲሰን እና ሉካስ ቤርግቫል በጉዳት ምክንያት አለመሰለፋቸው ለለንደኑ ክለብ መጥፎ ዜና ሆኗል። የፍጻሜው ጨዋታ አሸናፊ ማንም ይሁን ማንም የሁለቱ ክለቦች የዚህ ዓመት ብቃት ወደፊት በታሪክ መዝገብ አስከፊ በሚል መወሳቱ አይቀሬ ነው። የ44 ዓመቱ ጀርማናዊ ፍሊክስ ዝዋየር ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
ማንችስተር ሲቲ ለሻምፒዮንስ ተሳትፎ ያቀረበውን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል
May 20, 2025 71
አዲስ አበባ ፤ ግንቦት 12/2017(ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ቦርንማውዝን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኦማር ማርሙሽ፣ በርናርዶ ሲልቫ እና ኒኮ ጎንዛሌዝ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ኦማር ማርሙሽ ከርቀት አክርሮ በግሩም ሁኔታ ያስቆጠራት ጎል አስደማሚ ነበረች። ዳንኤል ጄቢሰን ለቦርንማውዝ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ማቴዎ ኮቫቺች ከማንችስተር ሲቲ፣ ሉዊስ ኩክ ከቦርንማውዝ በኩል በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብተዋል። ውጤቱን ተከትሎ የአምናው የሊጉ አሸናፊ ማንችስተር ሲቲ በ68 ነጥብ ደረጃውን ከ6ኛ ወደ 3ኛ ከፍ አድርጓል። በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ የተቃረበበትን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ማንችስተር ሲቲ በቀጣዩ እሁድ ከፉልሃም ጋር በሚያደርገው የመጨረሻ ሳምንት ጨዋታ ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ በሻምፒዮንስ ሊግ መሳተፉን ያረጋግጣል። በሊጉ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቦርንማውዝ በ53 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በማንችስተር ሲቲ 10 ዓመታት ያገለገለው የ33 ዓመቱ ቤልጂየማዊ ኮከብ ኬቨን ደ ብሮይን በኢትሃድ የመጨረሻ ጨዋታውን አድርጓል። ለተጫዋቹ የሽኝት መርሃ ግብር በኢትሃድ ተካሄዷል። ለዘጠኝ ወራት ከጉዳት ርቆ የነበረው የማንችስተር ሲቲው የባለንዶር አሸናፊ ሮድሪ ወደ ሜዳ ተመልሷል። በሌላኛው የ37ኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ክሪስታል ፓላስ ዎልቭስን 4 ለ 2 አሸንፏል። ኤዲ ኒኬቲያ ሁለት ጎሎችን ሲያስቆጥር ኤበሬቺ ኤዘ እና ቤን ቺልዌል ቀሪዎቹን ግቦች ለክሪስታል ፓላስ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ኢማኑኤል አግባዱ እና ዮርገንሰን ስትራንድ ላርሰን ለዎልቭስ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ክሪስታል ፓላስ በ52 ነጥብ 12ኛ፣ ዎልቭስ በ41 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዘዋል። የፊታችን እሁድ በሚጠናቀቀው የ2024/25 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሚሳተፉ ቀሪ ክለቦች እነማን ናቸው? የሚለው ጉዳይ አጓጊ ሆኗል።
የማንችስተር ሲቲ እና ቦርንማውዝ ተጠባቂ መርሃ ግብር 
May 20, 2025 99
አዲስ አበባ ፤ ግንቦት 12/2017(ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ከቦርንማውዝ ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ምሽት 4 ሰዓት ላይ በኢትሃድ ስታዲየም ይደረጋል። ማንችስተር ሲቲ በ65 ነጥብ 6ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቦርንማውዝ በ53 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ ከቀሪ ሁለት ጨዋታዎቹ አራት ነጥብ የሚፈልገው ማንችስተር ሲቲ የዛሬውን መርሃ ግብር ማሸነፍ በጣም ወሳኝ ነው። ለቦርንማውዝ ማሸነፍ ደረጃውን ከማሻሻል የዘለለ ትርጉም የለውም። በማንችስተር ሲቲ 10 ዓመታት ያገለገለው የ33 ዓመቱ ቤልጂየማዊ ኮከብ ኬቨን ደ ብሮይን በኢትሃድ የመጨረሻ ጨዋታውን ያደርጋል። ለተጫዋቹ የሽኝት መርሃ ግብር ተዘጋጅቶለታል።   በሌላኛው የ37ኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ክሪስታል ፓላስ ከዎልቭስ በተመሳሳይ ምሽት 4 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የኤፍኤ ካፕ ዋንጫ አሸናፊው ክሪስታል ፓላስ በ49 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ዎልቭስ በ41 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ጨዋታዎች ክሪስታል ፓላስ እና ማንችስተር ሲቲ በነበራቸው የኤፍኤ ካፕ የዋንጫ ጨዋታ ምክንያት በተስተካካይ መርሃ ግብር የተያዙ ናቸው።
አርሰናል ኒውካስትል ዩናይትድን በማሸነፍ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን አረጋገጠ
May 19, 2025 87
አዲስ አበባ ፤ ግንቦት 10/2017 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታ አርሰናል ኒውካስትል ዩናይትድን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዴክላን ራይስ በ55ኛው ደቂቃ የማሸነፊያዋን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አርሰናል ነጥቡን ወደ 71 ነጥብ ከፍ አድርጓል። መድፈኞቹ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መሳተፋቸውን አረጋግጠዋል። በ66 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ኒውካስትል ዩናይትድ በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመሳተፍ የመጨረሻ ሳምንቱን ጨዋታ አሸንፎ የሌሎችን ክለቦች ውጤት ይጠብቃል። በሌሎች የ30ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ሌላኛው የሻምፒዮንስ ሊግ ተፎካካሪ ኖቲንግሃም ፎረስት ዌስትሃም ዩናይትድን 2 ለ 1 በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ነጥቡንም ወደ 65 ከፍ በማድረግ 7ኛ ደረጃን ይዟል። ኤቨርተን ሳውዝሃምፕተንን እና ሌይስተር ሲቲ ኢፕስዊች ታውንን በተመሳሳይ 2 ለ 0 ሲያሸንፉ ፋልሃም ብሬንትፎርድን 3 ለ 2 ረቷል። በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ እንግሊዝን ወክለው የሚሳተፉ ቀሪ ክለቦች በቀጣዩ ሳምንት በሚደረጉ የ38ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ይለያሉ።
የአርሰናል እና ኒውካስትል ዩናይትድ የሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታ 
May 18, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2017(ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት አርሰናል ከኒውካስትል ዩናይትድ ጋር ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ላይ በኤምሬትስ ስታዲየም ይካሄዳል። አርሰናል በ68 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ኒውካስትል ዩናይትድ በ66 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። መድፈኞቹ በዛሬው ጨዋታ ቢያንስ አንድ ነጥብ ካገኙ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መሳተፋቸውን ያረጋግጣሉ። በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመሳተፍ አራት ነጥብ የሚያስፈልገው ኒውካስትል ዩናይትድ የዛሬው ጨዋታ ለአውሮፓ መድረክ ተሳትፎ ህልሙ ወሳኝ የሚባል ነው። ሌላኛው የሻምፒዮንስ ሊግ ቦታን ለማግኘት እየተፎካከረ የሚገኘው ኖቲንግሃም ፎረስት ወደ ለንደን ስታዲየም በማቅናት ከቀኑ 10 ሰዓት ከ15 ላይ ከዌስትሃም ዩናይትድ ጋር ይጫወታል። ኖቲንግሃም ፎረስት በ62 ነጥብ 7ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኤቨርተን ከሳውዝሃምፕተን ከቀኑ 8 ሰዓት፣ ብሬንትፎርድ ከፉልሃም እና ሌይስተር ሲቲ ከኢፕስዊች ታውን በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም