ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ለጉምሩክ አገልግሎት መቀላጠፍ ትልቅ ዕድል ይዞ መጥቷል
Jan 8, 2026 132
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018(ኢዜአ)፦ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ቀልጣፋ የጉምሩክ አገልግሎትን ለማጠናከር ትልቅ ዕድል ይዞ መምጣቱን የጉምሩክ ኮሚሽን አስታወቀ። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በስኬት መጠናቀቁን ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በይፋ ማስጀመራቸው ይታወቃል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል ዕድል መፍጠር እንዲሁም በዜጎችና በተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት ዋነኛ ዓላማዎቹ ናቸው። የጉምሩክ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሙሉ ወርቅ ደረሰ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ኮሚሽኑ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ ወቅት የንግድ እንቅስቃሴን የሚያሳልጡ፣ ኮንትሮባንድን ለመቆጣጠር የሚያስችሉና በአጠቃላይ የኮሚሽኑን ስራዎች የሚያሻሽሉ ቴክኖሎጂዎች ወደ ሥራ አስገብቷል። ቴክኖሎጂዎቹ ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ምርቶችን ክትትል ለማጠናከር፣ የሰው ንክኪና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል እንዲሁም ደንበኞች ባሉበት ሆነው አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችሉ ናቸው ብለዋል። በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የሚተገበረው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ደግሞ በጉምሩክ ዘርፍ የሚሰጡ አገልግሎቶችን ለማዘመን እና ለማቀላጠፍ ትልቅ እድል ይዞ መምጣቱን ጠቅሰዋል። ስትራቴጂውን ስኬታማ ለማድረግ የተቋማት ቅንጅት እንደ ዋነኛ የድጋፍ ማዕቀፍ መሆኑን በማንሳት፥ ኮሚሽኑ የበከሉን ይወጣል ብለዋል። በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዘ አሰራር ተግባራዊ መደረጉን ገልጸው፤ በሂደት ላይም ያሉ ቴክኖሎጂዎች በቀጣይ ወደ ስራ ይገባሉ ብለዋል። ምክትል ኮሚሽነሯ እንደገለጹት በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የጉምሩክ አገልግሎትን በቴክኖሎጂ የተደገፈ የማድረግ ሰራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ።
የኢትዮጵያ ሳተላይቶች ያመነጯቸው መረጃዎች ጉልህ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ አበርክተዋል
Jan 8, 2026 90
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሳተላይቶች ያመነጯቸው መረጃዎች ጉልህ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማበርከታቸውን የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ጂኦ ስፓሻል ኢንስቲትዩት ገለጸ። በሚቀጥለው ዓመትም ሶስተኛዋን የመሬት ምልከታ የመረጃ ሳተላይት ወደ ሕዋ ለማምጠቅ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል። የኢትዮጵያ የመጀመሪያዋን ሳተላይት ኢቲ-አር.ኤስ.ኤስ1 (ET-RSS1) እንዲሁም ሁለተኛው ኢቲ-ስማርት-አር.ኤስ.ኤስ (ET-SMART-RSS) የተሰኙ ሁለት የመረጃ ሳተላይቶችን ወደ ሕዋ ማምጠቋ ይታወሳል። የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ጂኦ ስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ቀደም ሲል ወደሕዋ የተላኩ ሁለት የመሬት ምልከታ ሳተላይቶች የአገልግሎት ጊዜያቸውን አጠናቀዋል። የመሬት ምልከታ የመረጃ ሳተላይቶቹም በርካታ ቴክኖሎጂያዊና ሳይንሳዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን ማበርከታቸውን ተናግረዋል። በዚህም የምግብ ዋስትና፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በተፈጥሮ ሃብት አያያዝ የግብርና መስኮች፣ በከተማ ፕላንና መሠረተ ልማት፣ በሀገር ሉዓላዊነትና ገጽታ ግንባታ ከፍተኛ ጠቀሜታ ማበርከታቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በሚቀጥለው ታኅሳስ 2019 ዓ.ም በምስል ጥራትና የጊዜ ቆይታ አቅም ያላት ኢቲ-አር.ኤስ.ኤስ 2 (ET-RSS2) የተሰኘች ሳተላይት ወደ ሕዋ ለማምጠቅ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። በቀጣይ የምትመጥቀው ኢቲ-አር.ኤስ.ኤስ 2 ሳተላይት ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመታጠቅ በሕዋ ላይ የአምስት ዓመታት የጊዜ ቆይታ እንዲኖራት ታሳቢ መደረጉ ነው የተገለጸው። ከዚህ ቀደም ወደ ሕዋ ከተላኩ ሳተላይቶች የተገኘውን መረጃ የመቀበል፣ የመተንተን፣ የመቆጣጠርና የጥገና አቅም መፈጠሩን አስረድተዋል። ሦስተኛዋን ሳተላይት ለማምጠቅ እየተደረገ የሚገኘው ጥረትም የኢትዮጵያን የሳተላይት ልማት አቅም በተግባር የሚያሳይ እንደሚሆን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ለሰው ሰራሽ አስተውሎት መሰረት እየጣለች ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jan 6, 2026 147
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የፖሊሲ ማዕቀፍ እና መሰረተ ልማትን ጨምሮ ለሰው ሰራሽ አስተውሎት መሰረት የሚጥሉ ስራዎችን እያከናወነች እንደምትገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን በማስመልከት በተዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ ጽሑፍ አቅርበዋል። በውይይት መድረኩ ላይ ከምሁራን ለቀረቡላቸው ጥያቄዎችም ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሰው ሰራሽ አስተውሎት (ኤ.አይ) በዓለም ደረጃ ያለው ተጽእኖ እና ድርሻ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል። በተጠናቀቀው የ2025 የፈረንጆቹ ዓመት ኤ.አይ በርካታ ስራዎችን መተካቱን አውስተው አሁንም በተጠናከረ መልኩ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። ፈጥነን ልጆቻችንን ካዘጋጀን ሰው ሰራሽ አስተውሎትን እንደ ተለያዩ ምርቶች በቀላሉ መጠቀም እንችላለን ብለዋል። ኤ.አይ ስራ ይቀማል ብዬ አልሰጋም ሲሉ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የሰው ልጅ መስራት የሰው ልጅ ሊሰራቸው የማይገባቸውን ስራዎች እየተካ ይሄዳል ነው ያሉት። ኤ.አይን የምንፈጥር እኛነን ኤ.አይን የምንቀይር እኛ ነን ቀድመን ግን ፋውንዴሽን መጣል ይገባናል ብለዋል። መንግስት ለሰው ሰራሽ አስተውሎት ፖሊሲ እና ስትራቴጂ አዘጋጅቶ እየተተገበረ መሆኑን ጠቅሰው ሳይንስ ሙዚየም አንዱ መሰረተ ልማት መሆኑን ተናግረዋል። መሰረተ ልማት እና ታለንት ለዘርፉ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱም ነው ያብራሩት። ኢትዮጵያ የምትገነባው የኤ.አይ ዩኒቨርሲቲም የኢትዮጵያን እና የአፍሪካን ብዙ ችግሮች ይፈታል ተብሎ እንደሚታመን ተናግረዋል። ዋናው ለልጆቻችን ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጆቻችን የሚወዳደሩበት ልጆቻችን ከሌላው አንስው የማይታዩበት ሁኔታ ለመፍጠርም እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ቀድሞ መወዳደር ቀድሞ መገኘት አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው ኤ.አይን በዛ መልክ ማየት እንደሚገባ ገልጸዋል። ኤ.አይ ስራዎችን በማቃለል እና ጊዜ በመቆጠብ ወሳኝ ድርሻ እንደሚወጡም ነው የገለጹት። ተማሪዎችም ኤ.አይን መጠቀም አለባቸው፤ ቴክኖሎጂዎቹን መጠየቅ እንዲችሉ አድርገን ከፈጠርናቸው ተማሪዎች ተወዳዳሪ መሆን እንደሚችሉ ገልጸዋል። የመጠየቅ ብቃት ችሎታ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚህ ረገድም ኤ.አይ የተማሪዎችን አቅም እንደሚገነባ ተናግረዋል። የመጀመሪያው ትውልድ ለኢኮኖሚ ቅድሚያ የሰጠ እና ሁለተኛው ትውልድ ፖለቲካዊውን ያስቀደመ መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአሁኑ ዘመን የሀሳብ ትውልድ እንደሆነም ጠቅሰዋል። ሀሳብ የሚወድ ትውልድ ችግሮች እየፈታ እና እያቀለለ እንደሚሄድም ተናግረዋል። ኤ.አይ ዝግጅት እና ስራ እንደሚፈልግ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ከመፍራት ይልቅ እውነታውን በመጋፈጥ ማሸነፍ እንችላለን ብለዋል።
ከተማርንና ዝግጁ ከሆንን በኤ አይ የማይናቅ ደረጃ ላይ እንደርሳለን-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jan 6, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 28/2018(ኢዜአ)፡- ከተማርንና ዝግጁ ከሆንን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሂደት የማይናቅ ደረጃ ላይ እንደርሳለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል በማስመልከት በተዘጋጀ የውይይት መድረክ ላይ ጽሑፍ አቅርበዋል። ጽሑፍ ካቀረቡ በኋላም ከምሁራን ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በዚሁ ወቅትም፤መንግሥት የኮሪደር ልማትና መንገድ ሠርቶ ለነዋሪው ሲያቀርብ ይህን በአግባቡ እንዴት መያዝ እንደሚቻል ደግሞ ምሁራን ከተሜነትን የሰው ልጅ ዐዕምሮ ላይ መሥራት ይጠበቅባችኋል ብለዋል። ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ጋር በተያያዘም ኢትዮጵያ ትልቅ ተስፋ ያላት ሀገር መሆኗን አንስተዋል። ኤ አይ ከሚፈልጋቸው ነገሮች አንዱ ኢነርጂ መሆኑን ጠቁመው፤ ከዚህ አንጻር ኢትዮጵያ ብዙ የማምረት ዐቅም እንዳላት አረጋግጠዋል። ኢነርጂ ላይ ኢንቨስት ካደረግን ለኤ አይ አንድ አስቻይ ጉዳይ ፈታን ማለት ነው ሲሉም ገልጸዋል። ሌላው ኤ አይ የሚፈልገው ጉዳይ መረጃ(ዳታ) እና የመረጃ ማዕከል(ዳታ ሴንተር) መሆኑንም አስገንዝበዋል። ከተማርን፣ ዝግጁ ከሆንን፣ እየሠራናቸው ያሉትንና በቀጣይ የምናከናውናቸውን ጨምሮ በመተባበር ለለውጥ ዝግጁ ሆነን በትጋት ከሠራን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሂደት የማይናቅ ደረጃ ላይ እንደርሳለን ብለዋል። ለኤ አይ ግብዓት የሚሆኑ ነገሮች በብዛት በአፍሪካ እንደሚገኙም አስገንዝበዋል።
ማዕከሉ በምርምር ያወጣቸውን የሰብል ዝርያዎችን ተደራሽ ለማድረግ የመነሻ ዘር ብዜት እያካሄደ ነው
Jan 5, 2026 174
ሮቤ፤ ታህሳስ 27/2018 (ኢዜአ)፦የሲናና ግብርና ምርምር መዕከል በምርምር ያገኛቸውን የተለያዩ የሰብል ዝርያዎች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ የመነሻ ዘር እያባዛ መሆኑን ገለጸ። ማዕከሉ አርሶ አደሮችና የባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ የመስክ ቀን ጉብኝት አካሂዷል። በመርሐግብሩ ላይ የተገኙት የምርምር ማዕከሉ ስራ አስኪያጅ አቶ ታመነ ሚደቅሳ እንዳሉት፤ማዕከሉ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በምርምር እየደገፈ ነው። በተለይ ማዕከሉ ባለፉት ዓመታት በስንዴ፣ ገብስና ሌሎች ስምንት የትኩረት መስኮች ላይ ተመስርቶ ምርምሮችን በማካሄድ 116 የምርምር ውጤቶችን ለተጠቃሚው ማድረሱን አስታውሰዋል። ማዕከሉ በቅርብ ጊዜ በምርምር ያወጣቸውን ዝርያዎች አርሶ አደሩ ጋር ተደራሽ እንዲሆኑ የመስራች ዘር የማባዛት ሥራ እያካሄደ መሆኑን ተናግረዋል። በሲናና አርሶ አደሮች በኩታገጠም አሰራር እየተባዛ ያሚገኘውና አርሶ አደሩ ልምድ እንዲለዋወጥ ዓላማ በማድረግ የተዘጋጀው የመስክ ምልከታ የዚሁ ጥረት አካል ነው ብለዋል። በማዕከሉ የግብርና ኤክስቴንሽን ተመራማሪ አቶ ባያታ ጋዲሳ በበኩላቸው፤ ማዕከሉ በምርምር የሚያወጣቸው የሰብል ዝርያዎች ውጤታማነታቸው ከተረጋገጠ በኋላ አርሶ አደሩ ጋር ተደራሽ እንደሚሆኑ አመልክተዋል። ዝርያዎቹ በስፋት ተጠቃሚው አርሶ አደር ጋር እንዲደርሱ በምርምር ማዕከሉና በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በማባዛት ተደራሽ እንደሚደረጉ አክሏል። አቶ ባያታ እንዳሉት፤ ማዕከሉ በአሁኑ የመኽር ወቅት በምዕራብ አርሲና በባሌ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች ከ150 ሄክታር በሚበልጡ የአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በቅርቡ ከማዕከሉ የተለቀቁ ዝርያዎችን እያባዛ መሆኑን አስረድተዋል። እየተባዙ ከሚገኙ ዝርያዎች መካከል በአንድ ሄክታር መሬት እስከ 72 ኩንታል ምርት የሚሰጥ ''ቦኩ'' የሚባል ስያሜ የተሰጠው የስንዴ ዝርያ እንደሚገኝበት አመልክተዋል፡፡ የመስክ ምልከታው ላይ የተሳተፉ አርሶ አደሮች በሰጡት አስተያየት፤ ማዕከሉ በአካባቢያቸው በመኖሩ የተሻለ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችን በየጊዜው በማግኘት ምርታማነታቸውና ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በ1978 ዓ.ም የተቋቋመው የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል እስከ አሁን 116 የሚሆኑ የሰብል፣ የእንስሳት መኖና ሌሎች የግብርና ቴክኖሎጂዎች ላይ ያተኮሩ ዝርያዎችን በምርምር በማፍለቅ ለተጠቃሚው ማሰራጨቱ ተገልጿል።
ክልሉ የሳይንስ እና ፈጠራ ክህሎት ያላቸውን ተማሪዎች በመደገፍ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እያደረገ ነው
Jan 5, 2026 178
አሶሳ፤ ታህሳስ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሳይንስ እና ፈጠራ ክህሎት ያላቸው ተማሪዎችን በመደገፍ ብቁና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው "የተማሪዎች የሳይንስ እና ፈጠራ ሥራ ለልማታችን እመርታ" በሚል መሪ ሃሳብ የተማሪዎችን የፈጠራ አቅም ለማሣደግ ያለመ የምክክር መድረክ በአሶሳ ከተማ አካሂዷል። በመድረኩ ላይ በተማሪዎች የተሰሩ የፈጠራ ስራዎች ለዕይታ ቀርበዋል። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ትምህርት ቢሮ የስርዓተ ትምህርት እና የተቋማት ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ሙሐመድ ኡስማን እንደገለፁት፣በሀገር ደረጃ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍን ለማሳደግ ለዘርፉ ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል። በዚህም ተማሪዎች ከትምህርታቸው ጎን ለጎን ችግር ፈቺ የፈጠራ ሥራዎችን በመስራት ራሳቸውን ከቴክኖሎጂ ጋር የሚያለማምዱበት ዕድል እየተፈጠረ ነው ብለዋል። በክልሉ በርካታ ተማሪዎች የተለያዩ የፈጠራ ስራዎችን በመስራት በሀገር አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ቢሮው የፈጠራ ክህሎት ላላቸው ተማሪዎች የተለያዩ መድረኮችን በማመቻቸት ስራዎቻቸውን እንዲያስተዋውቁ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ በተማሪዎች የፈጠራ ውድድር አሸናፊ ከነበሩት ተማሪዎች መካከል ተማሪ ብርሃኑ ሲሳይን እንደ ማሳያ ያነሱት አቶ ሙሐመድ፤ ሌሎች ተማሪዎችም ያላቸውን ተሰጥኦ እና ችሎታ በመጠቀም በሁሉም ዘርፍ ተወዳዳሪ መሆን እንደሚጠበቅባቸው መክረዋል። ተማሪ ብርሃኑ ሲሳይ በፀሐይ ሃይል የሚሰራ የውሃ መሳቢያ ሞተር መሥራቱን በማስታወስ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ አቶ ጌታቸው ፊሊጶስ በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በዲጂታል 2030 ያለመችውን ዕቅድ ለማሣካት ከትምህርት ቤት ጀምሮ በዘርፉ ትኩረት ሰጥቶ መሥራት ይገባል ብለዋል። ተማሪዎች ትልቅ ሀገራዊ ራዕይ ይዘው እንዲያድጉ እና የፈጠራ አቅሞቻቸውን አውጥተው ችግር ፈቺ ሥራዎችን እንዲሰሩ የሚያስችል የድጋፍና ክትትል ሥራ ከባለድርሻ አካላት እንደሚጠበቅም ገልጸዋል። በመድረኩ ላይ የፈጠራ ስራዎቻቸውን ላቀረቡ ተማሪዎች ዕውቅና ተሰጥቷቸዋል።
መፍትሔ አፍላቂ የቴክኖሎጂ ፈጣሪ ወጣቶች
Jan 5, 2026 97
በጀነራል ዊንጌት ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የማኑፋክቸሪንግ ትምህርት ክፍል አሰልጣኝ ወርቁ ፈንታሁን ከጓደኛው ጋር በመሆን በኢትዮጵያ ያለውን የዶሮ እርባታ ስራን ዘመናዊ ማድረግ የሚያስችል ቴክኖሎጂ ፈጥረዋል። ዘመናዊ የዶሮ ማርቢያ ቤት(ኬጅ) ለመፍጠር ያነሳሳቸው በባህላዊ መንገድ የሚከናወነውን አሰራር ለማዘመን በማሰብ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊው የዶሮ ኬጅ በተወሰነ አካባቢ ላይ በርካታ ዶሮዎችን ለማርባትና ዶሮዎቹን በንጹህ እና ጤንነታቸው በተጠበቀ ቦታ ማርባት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የሚገኘውን የእንቁላል ምርት ሳይሰበር በቀላሉ መሰብሰብ የሚቻልበትን እድልም ይፈጥራል ብለዋል። በቀጣይም ቴክኖሎጂው ለዘርፉ ውጤታማነት ከሚኖረው ፋይዳ አንጻር የማስተዋወቅና በስፋት ተመርቶ ወደ ገበያ እንዲቀርብ እንደሚሠሩ ጠቁመዋል። አካል ጉዳተኞችን በቀላሉ መመገብና ፈሳሽ ነገሮችን ማጠጣት የሚያስችል ሮቦት የሰራው ደግሞ በጀነራል ዊንጌት ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የኢንዱስትሪያል ኤሌክትሮኒክስ ቴክኖሎጂ የደረጃ አራት ተመራቂ ተማሪ ዳግም ጋርጠው ነው። ሮቦቱ ያለምንም የሰው ንክኪ አካል ጉዳተኞች በቀላሉ በሚጠቀሙበት መልኩ የተሠራ ነው ብሏል። ስራው ውጤታማ እንዲሆን ኮሌጁ የግብዓት፣ የሙያ እና ሌሎች ድጋፎች እንዳደረገለትም ተናግሯል። በኮሌጁ የቴክኖሎጂ ልማትና የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን አገልግሎት ምክትል ዲን ደሜ መርሻ በአሰልጣኞችና በሰልጣኞች ቅንጅት ውጤታማ የፈጠራ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል። የመኖ መፍጫ፣ የዘመናዊ ዶሮ ኬጅ እና የፕላስቲክ መፍጫና ማቀነባበሪያ እንዲሁም ፕላስቲኩን ወደ ተለያየ ምርት መቀየር የሚችሉ ማሽኖች በኮሌጁ ተሰርተው ጥቅም ላይ ከዋሉ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ውጤቶች መካከል መሆናቸውን አብራርተዋል። የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅርበት እየሰራ እንደሚገኝና ፈጠራዎቹን የማስተዋወቅ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር(ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ተቋማት ቴክኖሎጂ ፈጣሪ ባለሙያዎችን እንዲሁም ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን እንዲያመነጩ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ የምታስገባቸውን የተለያዩ የቴክኖሎጂ ውጤቶች በሀገር ውስጥ ለመተካት፣ አዳዲስ ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን የመፍጠር ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ገልፀዋል። በቴክኒክና ሙያ የሚሰሩ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ስራዎች በሀገር ልማት ላይ አበረታች ወጤት እያመጡ መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል። ኢንስቲትዩቱ ሀገራዊ የክህሎት ማበልፀጊያ ፕሮግራም ተግባራዊ በማድረግ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ያላቸውን ዜጎች ውጤታማ እንዲሆኑ ከተለያዩ አካላት ጋር በመሆን እየደገፈ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
የዲጂታል ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው ያስችላል
Jan 4, 2026 170
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦የዲጂታል ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው በማድረግ ትክክለኛ ፖሊሲ መቅረጽ የሚያስችል መሆኑን የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ገለጸ፡፡ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት በአዋጅ ቁጥር 1370/2017 መሰረት ከፌደራል እስከ ታችኛው የአስተዳደር እርከን ድረስ ራሱን የቻለ አደረጃጀት ያለው ሆኖ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የማከናወን፣ የመምራት፣ የማስተባበር፣ የመደገፍ፣ የምዝገባ መረጃዎችን የማስተዳደር እና የማደራጀት፣ በብሔራዊ ደረጃ በመረጃ ቋት አደራጅቶ የመያዝ ሀላፊነት ተሰጥቶታል። አገልግሎቱ በተሰጠው ስልጣን መሰረተ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ውክልና በመስጠት በመዲናዋ ሁሉም ወረዳዎች የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ማከናወን ጀምሯል፡፡ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቢቂላ መዝገቡ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የወረቀት አሰራርን በመቀየር አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው ያደርጋል፡፡ ከዚህ ቀደም በነበረው የማኑዋል/የወረቀት አሰራር አንድ ሰው ሁለት ቦታ የልደት፣ የሞትና መሰል የወሳኝ ሁነት የምስክር ወረቀት ያወጣ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ በዚህም በተጭበረበረ መረጃ የተሰሩ የወሳኝ ሁነት መረጃዎች መንግስት ለሚያሳልፋቸው የፖሊሲ ውሳኔዎች አስቸጋሪ ሆነው መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የባዮሜትሪክና ባዮግራፊክ መረጃ እንደሚይዝ ገልጸው፤ የባዮሜትሪክ መረጃዎችን ከብሔራዊ መታወቂያ ጋር እንዲተሳሰር ይደረጋል ብለዋል፡፡ በዚህም አንድ ሰው አንድ ሆኖ የሚታወቅባትን ኢትዮጵያ መፍጠር የሚያስችል እንቅስቃሴ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የባዮሜትሪክና ባዮግራፊክ መረጃዎችን በማቀናጀት የአንድን ሰው ትክክለኛ ማንነት የሚገልጹ መሆናቸውን የገለጹት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፤ የአንድን ሰው ዜግነት መለየትም ያስችላሉ ብለዋል፡፡ እነዚህ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ መረጃዎችን በኩነት ምዝገባና እና በብሄራዊ መታወቂያ /ፋይዳ/ አማካኝነት መሰብሰብ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ማከናወን የሚያስችል መተግበሪያ በኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት አማካኝነት ለምቶ ወደ ሥራ መግባቱንም ተናግረዋል፡፡
የዲጂታል ግብይት ሥርዓት የንግድ እንቅስቃሴን አቀላጥፏል
Jan 4, 2026 104
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እያደገ የመጣው የዲጂታል ግብይት ሥርዓት የንግድ እንቅስቃሴን ከማቀላጠፍ ባለፈ ከመጭበርበርና ከእንግልት እየታደጋቸው መሆኑን የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ። ነዋሪዎቹ መጪዎቹን የገና እና የጥምቀት በዓላት ግብይታቸውን በቴሌብር እና በሞባይል ባንኪንግ በመጠቀም ያለምንም እንግልት እያከናወኑ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት መካከል አቶ ገዛህኝ መካሻ እንደገለጹት፤ የዲጂታል ግብይት ሥርዓቱ በፈጠረው ምቹ ሁኔታ ማንኛውንም ክፍያ በቴሌብርና በሞባይል ባንኪንግ እንደሚፈጽሙ ገልጸዋል። ይህም ጉልበትንና ጊዜን ከመቆጠብ ባለፈ፣ ተንቀሳቃሽ ገንዘብ በመያዝ ከሚገጥሙ ስጋቶችና ከአጭበርባሪዎች ራሳቸውን ለመከላከል እንዳስቻላቸው ጠቁመዋል። በመሆኑም ለመጪዎቹ በዓላት የሚገዟቸውን ቁሳቁሶች በዲጂታል መንገድ እየፈጸሙ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ዶክተር ሳሮን ሲሳይ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል የነበሩ የክፍያ አገልግሎቶች በእንግልት የተሞሉና ጊዜን በአግባቡ ለመጠቀም የማይመቹ እንደነበሩ አስታውሰዋል። አሁን ላይ ግን እያንዳንዱን አገልግሎት በዲጂታል መንገድ መፈጸም መቻሉ ሕይወትን በእጅጉ ቀለል እንዳደረገው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እያሳየች ያለውን ፈጣን ዕድገት ለማስቀጠል የዲጂታል ዓለምን መቀላቀሏ የሚያስደስት መሆኑን የገለጹት ደግሞ መምህርት ፍሬሕይወት ለማ ናቸው። የዲጂታል ግብይት ሥርዓቱ ጥሬ ገንዘብ የመያዝ ልማዴን በማስቀረት ሁሉንም አገልግሎት በስልኬ እንዳገኝ አስችሎኛል ሲሉም አክለዋል። የኢትዮ ቴሌኮም የሞባይል መኒ ቢዝነስ ዋና ኦፊሰር አቶ ብሩክ አድሃና፤ ተቋሙ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የዲጂታል ሕልም እውን ለማድረግ በትጋት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል። እንደ ኦፊሰሩ ገለጻ፤ባለፉት አራት ዓመታት ከሀምሳ ሰባት ሚሊዮን በላይ በሆኑ የዲጂታል ክፍያ ደንበኞች አማካኝነት ከስድስት ትሪሊዮን ብር በላይ ግብይት ተከናውኗል። መጪዎቹን የገናና የጥምቀት በዓላት ምክንያት በማድረግም ደንበኞች የዲጂታል ግብይቶችንም ሆነ ሌሎች አገልግሎቶችን ያለምንም መቆራረጥ እንዲያከናውኑ አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን አረጋግጠዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት መረጋገጥ የላቀ ሚና ይጫወታል
Jan 4, 2026 105
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት ይበልጥ መረጋገጥ የላቀ ሚና እንደሚጫወት የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ ገለጹ፡፡ የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ፤ ጥራት ያለውና ፍትሐዊ የትምህርት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የዲጂታል ቴክኖሎጂን አማራጮች በአግባቡ መጠቀም ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ ዓለም አቀፋዊውን የዕድገት ፍጥነት ተከትሎ በትምህርት መስኩ ዕውቀትና ክህሎቱ የዳበረ ማኅበረሰብን ለመፍጠር ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ጉልህ አሻራ አሳርፏል ነው ያሉት። በተለይም የመማር ማስተማር ሂደቱን በማዘመንና የፈተና አሰጣጥ ሥርዓቱን ዲጂታላይዝ በማድረግ የፈተና ደኅንነት እንዲጠበቅ ማድረጉንም ገልጸዋል፡፡ ስትራቴጂው ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሀገሪቱን የዲጂታላይዜሽን ጉዞ የሚደግፉ የሥልጠና መስኮችን እንዲከፍቱና በዘርፉ ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት የሚያስችሉ ግብዓቶች እንዲሟሉ ምቹ መደላድል መፍጠሩንም አክለዋል። መንግሥት የሀገሪቱን ብልጽግና ለማረጋገጥ የጀመረውን የማዘመን ሥራ ይበልጥ ለማሳለጥ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ተግባራዊ ማድረጉንም ገልጸዋል፡፡ ይህ ስትራቴጂ ዜጎች በዲጂታል ቴክኖሎጂ አማራጮች ታግዘው ባሉበት ቦታ ሆነው እንዲማሩ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ስትራቴጂው የትምህርት ተደራሽነትን ከጥራት ጋር በማጣመር ረገድም የላቀ ፋይዳ እንደሚኖረው ጠቁመዋል፡፡ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራትና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ከኢንዱስትሪው ጋር ይበልጥ ለማቀራረብ በትኩረት ይሠራል ብለዋል፡፡ ይህም ተማሪዎች በቴክኖሎጂው ረገድ ተግባር ተኮር ዕውቀትና ክህሎት እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። በተጨማሪም በዲጂታላይዜሽን ዙሪያ የሚከናወኑ የምርምር ውጤቶች ለተግባራዊ ጥቅም እንዲውሉ በማድረግ የትምህርት ዘርፉ ለስትራቴጂው ስኬት የሚጠበቅበትን ሀገራዊ ኃላፊነት እንደሚወጣ አረጋግጠዋል።
ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ኢትዮጵያ ለያዘችው የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬታማነት ቁልፍ ሚና አለው
Jan 4, 2026 106
ጅግጅጋ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ኢትዮጵያ ለያዘችው የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬታማነት ቁልፍ ሚናን የሚጫወት መሆኑን የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና አስተባባሪ ዮዳሄ አርአያስለሴ ገለጹ። የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም 2ኛው ዙር "ፋይዳ ለኢትዮጵያ" በሚል መሪ ሐሳብ የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ በጅግጅጋ ከተማ ተካሄዷል። በመርሃ ግብሩ መክፈቻ ላይ የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና አስተባባሪ ዮዳሄ አርአያስለሴ እንደገለጹት፤ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ኢትዮጵያ ለያዘችው የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬታማነትም ቁልፍ ሚናን የሚጫወት ነው። ዜጎች ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያን በመውሰድ የዜግነት መብታቸውን መጠቀም እንዳለባቸውም ጥሪ አስተላልፈዋል። የሱማሌ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኢብራሂም ኡስማን፤ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ለሀገር ዕድገት ያለው ጠቀሜታ ከፍተኛ እንደሆነ ገልጸው በክልሉ ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡ ለዜጎች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶችን ተደራሽ ለማድረግ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ አስፈላጊ በመሆኑ ሁሉም ዜጋ እንዲወስድ ሃላፊው አሳስበዋል። የዛሬው የሩጫ ውድድርም የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ሂደትን ከማነቃቃት ባለፈ በስፖርት ተወዳዳሪ ወጣቶችን ለማፍራት ትልቅ ዕድል መሆኑን አንስተዋል። በጎዳና ላይ የሩጫ ውድድሩ የክልሉ አመራሮች፣ አትሌት ኮማንደር ደራርቱ ቱሉ፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ አትሌቶች እና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እንዲሁም የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
የኢትዮ-ቴሌኮም ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬት ገንቢ ሚና ይወጣል
Jan 3, 2026 137
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮ-ቴሌኮም ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬት ገንቢ ሚና እንደሚወጣ የኢትዮ-ቴሌኮም ቺፍ ቴክኖሎጂ ኦፊሰር ታሪኩ ደምሴ ገለጹ። ኢትዮ ቴሌኮም 130ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን በማስመልከት ያዘጋጀውን ሁለት ዘመናዊ የኤሌክትሪክ መኪና ሽልማቶች ለአሸናፊ ደንበኞቹ አስረክቧል፡፡ ኩባንያው በሽልማት መርሃ-ግብሩ ላይ ተጨማሪ ስድስት ዘመናዊ መኪኖችን የሽልማት ዕጣዎችን የማውጣት ሥነ-ሥርዓት አከናውኗል፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም በዚህ የሽልማት መርሃ-ግብር ከዚህ ቀደም አራት የኤሌክትሪክ መኪኖችን እንዲሁም 13 ባለሶስት እግር ተሽከርካሪዎችን ለባለ ዕድለኛ ደንበኞቹ ማስረከቡን ገልጿል፡፡ በተጨማሪም 372 ዘመናዊ ስማርት ስልኮችንና የቴሌብር ኤሌክትሮኒክስ ገንዘብን ጨምሮ በሽልማት መርሐ ግብሩ ከ127 ነጥብ 8 ሚሊየን ብር በላይ አጠቃላይ ዋጋ ያላቸውን ሽልማቶች ሰጥቷል። የኢትዮ ቴሌኮም ቺፍ ቴክኖሎጂ ኦፊሰር ታሪኩ ደምሴ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ እውን ለማድረግ የጀመራቸውን ሰፋፊ ስራዎች አጠናክሮ በማጠናከር የበኩሉን ገንቢ ሚና እንደሚወጣ ተናግረዋል፡፡ የኢትዮ 130 ሜጋ ፕሮሞ እና ኢትዮ 131 ላኪ ስሎት ሽልማት ላይ እድለኛ የሆኑት አሸናፊዎች በሽልማቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል፡፡ ካነጋገርናቸው ባለእድለኞች መካከል ከጅማ ከተማ የመጡት ጥንዶች በጅማ ከተማ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሰራተኛ የሆነው ሳሙኤል ጣፋ እና ባለቤቱ ኢሌኒ ለማ ሽልማቱ ድርብ ደስታን እንደፈጠረላቸው ይገልጻሉ፡፡ ሌላው ባለ እድለኛ ገብረ ህይወት ታምር በበኩሉ ኢትዮቴሌኮም የኢትዮ 130 ሜጋ ፕሮሞ እና ኢትዮ 131 ላኪ ስሎት ሽልማት ዕድለኛ በመሆኑ መደሰቱን ተናግሯል፡፡ ኩባንያው በቀጣይም ደንበኞቹን ተሸላሚ የሚያደርገውን ቴሌ ፕለይ የተሰኘ የሽልማት መርሐ ግብሩን እንደሚያስቀጥልም ተገልጿል። በዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የኢትዮ-ቴሌኮም ከፍተኛ አመራሮች፣ የኢትዮጵያ ሎተሪ አገልግሎት ተወካዮች፣ የሚዲያ አጋሮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል።
ኢንስቲትዩቱ ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅና በማበልፀግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት አሳድጓል
Jan 3, 2026 174
ወልቂጤ ፤ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ):-የኢትዮጵያ የባዮ እና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ እና በማበልፀግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ የእንሰት መፋቂያና ማቀነባበሪያ ማሸን በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ በሰስየ ቀበሌ ለሚገኙና በማህበር ለተደራጁ አርሶ አደሮች አስረክቧል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ካሳሁን ተስፋዬ እንዳሉት ኢንስቲትዩቱ የማህበረሰቡን ኑሮና የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴ የሚያቀሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እያፈለቀ እና እያበለጸገ ይገኛል። ከዚህ ቀደምም የአቮካዶ ዘይት መጭመቂያ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለሲዳማ ክልልና ለደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል እንዲሁም የበቆሎ መሸልቀቂያ ማሽን ለምስራቅ ጉራጌ ዞን ተጠቃሚዎች ማስተላለፉን ተናግረዋል። አሁን ላይ ጥራቱን የጠበቀ የእንሰት መፋቂያና ማብላያ ማሽን በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ የሰስየ ቀበሌ በማህበር ለተደራጁ 15 ወጣቶች ማቅረብ ችሏል ነው ያሉት። ማሽኑ የጊዜና የጉልበት ብክነትን በመቀነስ የቆጮ እና ቡላ ማብላያ ሂደትን ከማሳጠር ባለፈ የተሻለ ምርት የሚያስገኝ መሆኑን ገልጸዋል። የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሳይንስ፣ ኢንፎርሜሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰላሙ አማዶ፣ ከእንሰት ምርት ምግብ በማዘጋጀቱ ሂደት የሴቶች ጫና ይበዛ እንደነበር ጠቅሰው ማሽኑ ወንዶች ጭምር በስራው እንዲሳተፉ የሚያስችል ነው ብለዋል። በዚህ ማሽን ከቆጮና ቡላ ባለፈ ሌሎች ምግቦችን ማዘጋጀት እንደሚቻል አመልክተው፤ ማሽኑ ለብዙዎች የሥራ ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል። ማሽኑን በክልሉ እንሰት አምራች አካባቢዎች ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የእንሰት ሰብል ዝርያን በማሻሻል ምርታማነትን በማሳደግ የአምራቹን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት ይሰራል ያሉት ደግሞ የጉራጌ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ ናቸው። ችግር ፈቺ የሆነ የእንሰት መፋቂያ እና በአጭር ጊዜ ያለ ብክነት ወደ ምርት የሚቀይሩ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ለህብረተሰቡ ተደራሽ እንዲሆኑም አስተዳደሩ ድርሻውን ይወጣል ብለዋል። በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ የሰስየ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አዲሱ ምስጎ፤ የተሰጣቸው ማሽን የእንሰት መፋቂያ፣ የአሚቾ ማድቀቂያ እና የቡላ መጭመቂያ መሆኑን ተናግረዋል። ማሽኑ በቀን አስከ 40 እንሰት መፋቅ የሚያስችል ሲሆን ይህም ተጠቃሚነታቸውን የበለጠ የሚያሳድግ መሆኑን ጠቁመዋል። ወይዘሮ ይስሬሽ ሰክት በበኩላቸው ማሽኑ እንሰት ፍቆ ለምግብነት ለማዋል የሚባክነውን ጊዜ እና ጉልበት የሚቀንስ መሆኑንም አንስተዋል።
የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር አማራጭ ቅንጦት ሳይሆን የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሀገር ሉዓላዊነት የማስከበሪያ መሠረት ነው - ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ
Jan 3, 2026 228
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2017(ኢዜአ)፦ የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር አማራጭ ቅንጦት ሳይሆን የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሀገር ሉዓላዊነት የማስከበሪያ መሠረት መሆኑን የኢፌዴሪ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ገለጹ። “የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረም ልዕልና ለሀገር ሉዓላዊነት” በሚል መሪ ሃሳብ በሀገር አቀፍ ደረጃ የመጀመሪያ የሆነ የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር አውደ ጥናት በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) ዋና መስሪያ ቤት ዛሬ ተካሂዷል፡፡ ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በወቅቱ እንደገለጹት፤ ኤሌክትሮኒክ ዋርፌር አማራጭ ቅንጦት ሳይሆን የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሀገራት ሉዓላዊነት መሠረት ነው። በዚህ ዘመን የሀገራት ኃይል መገለጫዎች በከፍተኛ ፍጥነት እየተቀያየሩ የመጡበት ወቅት መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም ሀገራት ሉዓላዊነታቸውን ለማስከበር በመሬት፣ በባሕር፣ በአየርና በሕዋ ክልል ውስጥ በሚደረጉ ፍልሚያዎች ብቻ ይጠቀሙ እንደነበረም ገልጸዋል። ዛሬ ዘመናዊ ውጊያ የሚካሄደው በማይታይ እና የጦርነቱን ዕጣ ፈንታ በሚወስን ረቂቅ የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረም ምህዳር ውስጥ መሆኑንም አብራርተዋል። ከዚህ አኳያ የኢትዮጵያ የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረምን መጠቀም የደህንነት ብቻ ሳይሆን የህልውና ጉዳይም ጭምር መሆኑን ገልጸዋል። የሀገራችን ሰፊ የቆዳ ስፋት እና ተለዋዋጭ ቀጣናዊ ጂኦ ፖለቲካዊ ሁኔታ ካለን ተጨባጭ የመከላከል አቅም ጋር መጣጣም ይኖርበታል ሲሉም አስገንዝበዋል፡፡ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ በበኩላቸው፤ የዘመኑ ጂኦ ፖለቲካዊ ፉክክር መልክ እየቀየረ መምጣቱን ገልጸዋል። የሀገር ሉዓላዊነት የሚረጋገጠው በመሬት፣ በባህር፣ በአየር፣ በሕዋ ወይም በሳይበር ላይ በሚደረግ ተጋድሎ ብቻ ያለመሆኑን አመልክተው፤ በማይዳሰስና በረቂቁ የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረም እንደሆነ ጠቅሰዋል። ዛሬ የተዘጋጀው አውደ ጥናት ይህንን የፉክክር ዘርፍ በብቃት ለመረዳትና በስፔክትረሙ ላይ አስተማማኝ የበላይነትን ለመጨበጥ የሚያስችል ብሔራዊ አቅም ለመገንባት መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለሚገጥሟት ዘመናዊ የጸጥታ ስጋቶች የምትሰጠው ምላሽ በሳይንሳዊ ትንታኔ እና በተቋማዊ ቅንጅት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ገልጸው፤ ለዚህም የተቋማት አመራር ቁርጠኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። በየተቋማቱ የሚገኙ እምቅ አቅሞችን መደመርና ቅንጅት መፍጠር ትኩረት እንደተሰጠው አብራርተዋል። የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀኔራል አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት፤ የሀገራት ደህንነት የሚረጋገጠው መረጃን ቀድሞ የማግኘት፣ ስፔክትረሙን የመቆጣጠርና ጠላት እንዳይጠቀምበት የማድረግ የቴክኖሎጂ የበላይነትን በመያዝ ነው። ይህንን ምህዳር የተቆጣጠረ ወገን መረጃን ቀድሞ የማግኘት፣ ውሳኔን በፍጥነት የመወሰንና የድል ልዕልናን የመያዝ ስትራቴጂካዊ ብልጫ እንደሚኖረውም አስረድተዋል። በመድረኩ ላይ የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር ታሪካዊ ዳራ፣ አሁናዊ የሀገራት ተሞክሮ፣ እንዲሁም የኢትዮጵያ ወቅታዊና መጻኢ ሁኔታዎችን የዳሰሰ መነሻ ጽሁፍ በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ዳንኤል ጉታ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል፡፡ በአውደ ጥናቱ ላይ የተለያዩ ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች የተገኙ ሲሆን፤ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ፣ የኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ፣ በመከላከያ መረጃ ዋና መምሪያ የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር መምሪያ ኃላፊ ኮሎኔል ዶክተር አሸናፊ ኦሊ፣ እንዲሁም የመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ግሩፕ ኃላፊ አቶ ጌታቸው ኃይለማርያም በፓናሊስትነት ተሳትፈዋል፡፡ በፓናል ውይይቱ በዋናነት የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረምን በአግባቡ በመቆጣጠርና በመምራት የኢትዮጵያን አሁናዊና መጻኢ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ዘርፉን የሚመራ ተቋም መገንባት፣ በዘርፉ የሚካሄዱ ጥናትና ምርምሮችን ማላቅ፣ እንዲሁም በባለድርሻ ተቋማት መካከል ያለውን ትብብርና ቅንጅት ይበልጥ ማሳደግ እንደሚያስፈልግ ተመላክቷል፡፡
የግብይት ሥርዓቱን ዲጂታላይዝ ለማድረግ የተጀመሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው
Jan 3, 2026 135
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ)፦ የግብይት ሥርዓቱን ዲጂታላይዝ ለማድረግ የተጀመሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። በሚኒስትሩ የተመራ የልዑክ ቡድን በከተማዋ ተዘዋውሮ የንግድ እንቅስቃሴ ቅኝት አድርጓል። በዚሁ ጊዜ ተቋማቸው በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የተያዙ ግቦች እንዲሳኩ የድርሻውን እየተወጣ ነው ብለዋል። የወጪ ንግድ ኮንትራትና የፍቃድ አሰጣጡን ሙሉ ለሙሉ በዲጂታል ሥርዓት መቀየሩን ገልጸው፣ የዲጂታል ግብይት እንዲሳለጥም ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ለአብነትም በአንድ ወር ብቻ ጤፍ በዘመን ገበያ የ53 ሚሊዮን ብር ግብይት መፈጸሙን አንስተዋል። መንግስት የዲጂታል ግብይትን ለማሳለጥ በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ወደ ዲጂታል ግብይት እንዲገቡ ይደረጋል ብለዋል። እንደ ሚኒስትሩ ማብራሪያ በቁም እንሰሳት ንግድ ላይ የደላላ ጣልቃገብነት በመቀነስና አሰራሩን በማዘመን የተሻለ አፈጻጸም ተመዝግቧል። የቁም እንስሳት የግብይት ማዕከላትን በማስፋት የግብይቱን ሥርዓት ግልጽና ዘመናዊ መደረጉን ገልጸው፤ከቁም እንስሳት ወጪ ንግዱ ገቢ እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በ2018 በጀት ዓመት ስድስት ወራት ከቁም እንስሳት ወጪ ንግድ ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱንም ነው የተናገሩት። በ2018 በጀት ዓመት ከቁም እንስሳት ወጪ ንግድ 70 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት ታቅዷል።
በክልሉ በዲጂታል አሰራር የተደገፉ አገልግሎቶችን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
Jan 3, 2026 88
አርባ ምንጭ፤ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በዲጂታል አሰራር የተደገፉ አገልግሎቶችን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት መደረጉ ተገለጸ፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የስራ አፈጻጸም ግምገማ በአርባ ምንጭ ከተማ ዛሬ ተካሄዷል። በመድረኩ ላይ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የስራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) በክልሉ ዲጂታል 2030ን በማሳካት የህዝቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሠራ ይገኛል። ''ከዲጂታል ቴክኖሎጂ ውጭ የሚታሰብ መንግስታዊ አገልግሎት አይኖርም'' ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ፥ ወረቀት አልባ አገልግሎቶችን በማስፋፋት ህዝቡን ከእንግልትና ከአላስፈላጊ ወጪ ለማዳን በትኩረት ይሰራል ብለዋል። ከሁሉም በላይ በክልሉ በዲጂታል አሰራር የተደገፉ አገልግሎቶችን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቷል ነው ያሉት። የፋይዳ መታወቂያ ዜጎችን ከተለያዩ አገልግሎቶች ጋር በማስተሳሰር ህይወትን በእጅጉ የሚያቀል በመሆኑ ዜጎች የዚሁ ትሩፋት ተጠቃሚ ለመሆን ፋይዳ መታወቂያ መያዝ እንዳለባቸውም ገልጸዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ ቦጋለ ቦሼ (ዶ/ር) የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን ለማሳካት በተደረጉ ጥረቶች ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት መከናወናቸውን አስረድተዋል፡፡ በክልሉ የተጀመሩ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እና የዲጂታል መታወቂያ ስራዎች ጉልህ ፋይዳ አላቸው ብለዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ዕቅድ ለማሳካት ክልሉ ድርሻውን እንዲጫወት ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እንደሚሠራም ጠቁመዋል። በመድረኩ የክልልና የዞኖች እንዲሁም የከተማ አስተዳደሮች ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ታድመዋል።
በከተሞች ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ የዲጂታል አገልግሎቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jan 3, 2026 82
ሆሳዕና ፤ ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ) ፡- በከተሞች ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ የዲጂታል አገልግሎቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተመላከተ፡፡ የቢሮ ኃላፊዎቹ እንደገለፁት፤ በከተሞች ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ የዲጂታል አገልግሎቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ ለኢዜአ እንዳሉት በክልሉ ከተሞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ በማደራጀት ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እየተሰራ ነው፡፡ የመደመር መንግሥት እይታን በመተግበር ዜጎች ባሉበት ሆነው በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ ለማስቻል ስማርት ከተሞችን መፍጠር ላይ ትኩረት መሰጠቱን ጠቁመዋል፡፡ በዚህም በክልሉ ዘጠኝ ከተሞች የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎትን ዲጂታላይዝድ በማድረግ ፈጣንና ከብልሹ አሰራር የጸዳ አገልግሎት እየተሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በቀጣይም ተግባሩን በማስፋት በ15 ከተሞች ለማስጀመር ቅድመ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የሲዳማ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብሩክ ሰለሞን በበኩላቸው በከተሞች ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ይነሱ የነበሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ተግባራዊ መደረጉን አንስተዋል። በተለይም የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ብልሹ አሰራሮችን ለማረምና የተገልጋይ እርካታን ለመጨመር መሰራቱን ጠቁመዋል፡፡ አገልግሎቱን ለማስፋትም የመቶ ቀናት እቅድ መዘጋጀቱንም ጠቁመዋል፡፡ በክልሉ የመንግሥት አገልግሎትን የተቀላጠፈ ለማድረግ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በሰመራ ከተማ መጀመሩን የገለፁት ደግሞ የአፋር ክልል ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኢንጂነር ጎቦኦ መሀመድ ናቸው። በዚህም ቀደም ሲል በከተማ አገልግሎት አሰጣጥ የነበሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቀነስ መቻሉን አንስተዋል። አገልግሎቱን በማስፋትም በክልሉ አዋሽን ጨምሮ በሌሎች ከተሞች ተደራሽ በማድረግ ተገልጋዩን ለማርካት መታቀዱን ገልፀዋል፡፡ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በበኩላቸው መንግሥት በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ሪፎርሞች መተግበሩን ተናግረዋል፡፡ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥ መዘመንም የማህበረሰቡን እንግልት ለመቅረፍ የተጀመረዉ ጥረት አካል መሆኑን ጠቁመዋል። ለዚህም በዲጂታል የታገዘ አገልግሎትን እስከ ቀበሌ መዋቅር በማስፋት በዘርፉ የሚነሱ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ አመራሩ ትኩረት ሰጥቶ ሊሰራ እንደሚገባም ሚኒስትሯ አሳስበዋል፡፡ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር የገጠር ትራንስፎርሜሽንን መሰረት ያደረገ ሀገራዊ የንቅናቄ መድረክ በሆሳዕና ከተማ ማካሄዱን መዘገባችን ይታወሳል።
የአብርሆት ቤተ-መጻሕፍትን ወደ ላቀ የዲጂታል ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ሦስት ታላላቅ የቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶች ይፋ ሆኑ
Jan 3, 2026 119
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ)፦የአብርሆት ቤተ-መጻሕፍትን ወደ ላቀ የዲጂታል ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ሦስት ታላላቅ የቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶች ዛሬ በይፋ የማስጀመር ተግባር ተከናውኗል። ይህንንም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት በመገኘት የቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶችን ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። ከንቲባ አዳነች፥ አቤቤ የአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት በመዲናዋ የንባብና የምርምር ባህል ማዕከል ሆኖ ስራ ከጀመረ አራት ዓመታት መቆጠራቸውን ገልጸዋል። ዛሬ በቤተ-መጻሕፍቱ በመገኘትም፥ ተቋሙን ወደ ላቀ የዲጂታል ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ሦስት ታላላቅ የቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶችን በይፋ ማስጀመራቸውን ጠቁመዋል። በዓመት በአማካይ ለ1 ነጥብ 8 ሚሊዮን አንባቢዎች አገልግሎት እየሰጠ የሚገኘውን ይህንን ተቋም ይበልጥ ለማዘመን የሚያስችሉ፦ የተቀናጀ የቤተ-መጻሕፍት አስተዳደር ሥርዓት፣ ዘመናዊ የዲጂታል ቤተ-መጻሕፍት እና ዓለም አቀፍ የምርምር መድረክ (Research Portal) በይፋ ሥራ እንዲጀምሩ መደረጉን አመልክተዋል። አገልግሎቶቹ አብርሆት በአዲስ አበባ ብቻ የተገደበ እንዳይሆን ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥሩ የተናገሩት ከንቲባዋ ማንኛውም ተማሪም ሆነ ተመራማሪ በየትኛውም የኢትዮጵያ አካባቢ ሆኖ የአብርሆትን የዕውቀት ማዕድ መቋደስ እንዲችል ያደርጋሉ ነው ያሉት። በተጨማሪም የታሪክ ሰነዶችን በዲጂታል መንገድ ተጠብቀው ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፉ ትልቅ እገዛ እንደሚኖራቸውም አክለዋል። ከንቲባዋ ቴክኖሎጂዎቹን በማልማት አስተዋጽኦ ላበረከቱ ባለድርሻ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
የስማርት አዳማ ፕሮጀክት ግቦችን ለማሳካት ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቷል
Jan 2, 2026 190
አዳማ፤ ታህሳስ 24/2018(ኢዜአ)፦ የስማርት አዳማ ፕሮጀክት ግቦችን ለማሳካት ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ማስፋፋት ላይ ትኩረት መሰጠቱን የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ ገለፁ። በአዳማ ከተማ ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማጠናክርና ህብረተሰቡን የፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ ያለመ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ በወቅቱ እንደገለፁት የስማርት አዳማ ፕሮጀክትን ለማሳካት የሚደረገው ጥረት አካል የሆነው ፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቷል። ይህም የከተማዋን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶች ዲጂታላይዝድ በማድረግ ህብረተሰቡ ባለበት ቦታ ሆኖ የመንግስት አገልግሎትን በተቀላጠፈና አስተማማኝ በሆነ መንገድ ለማግኘት ያግዛል ብለዋል። የመንግስት አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝድ ማድረግ ተገልጋዩ ከመሬት ሀብት አስተዳደርና አጠቃቀም ጋር የሚያነሳቸው ጥያቄዎችን፣ የገቢ ግብር፣ የትራንስፖርት አገልግሎትና የከተማዋን ፀጥታ በካሜራ በመቆጣጥር ምላሽ መስጠት እንደሚያስችል ጠቁመዋል። የስማርት ሲቲ አካል የሆነው የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሁሉንም አገልግሎቶች ዲጂታላይዝድ በማድረግ በአንድ ቦታ ለማግኘት የጎላ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ብለዋል። የዲጂታል ቴክኖሎጂው ስርአትም ሌብነትና የመሬት ምዝበራን በማስቀረት የከተማዋን ገቢ በማሳደግ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማቶች እንዲሳለጡ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። በውይይቱ ከተሳተፉ የአዳማ ከተማ ነዋሪ ሀሰን ጂማ እንደገለፁት የከተማዋ የዲጂታል አገልግሎት ጊዜና ገንዘባቸውን ቆጥቦላቸዋል። ዲጂታል አገልግሎቱ ከፋይዳ መታወቂያ ጋር መተሳሰሩ ቀደም ሲል በከተማዋ ይስተዋሉ የነበሩ ብልሹ አሰራሮችን በመቅረፍ የተሻለ አገልግሎት እንድናገኝ የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ በላቸው ደምሴ ናቸው።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት ነው
Jan 2, 2026 117
ወልዲያ፤ ታህሳስ 24/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት መሆኑን የኢንፎርሜሽ ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ታኅሣሥ 11 ቀን 2018 ዓ.ም የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ስትራቴጂ ይፋ በማድረግ የዲጂታል 2025 ክንውን ደግሞ በስኬት መጠናቀቁን መግለፃቸው ይታወሳል። በሰሜን ወሎ ዞን ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂና የኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት መሆኑን ገልጸዋል። የአይሲቲ ባለሙያ የሆኑት ታደሰ አብዬ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በዘርፉ ጽኑ መሰረት ያኖረ ስኬታማ ስራ መሆኑን ተናግረዋል። የስትራቴጂው መተግበር በበርካታ ተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥና የአሰራር ቅልጥፍናን፣ የቁጥጥርና ተጠያቂነት አሰራርን በማስፈን እንዲሁም ብልሹ አሰራርን መከላከል አስችሏል ብለዋል። ይህም ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በማሳካት የአገራችንን ሁለንተናዊ እድገት ዳር ለማድረስ መሰረት የጣለ በመሆኑ በጋራ ልንረባረብ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። የኮሙኒኬሽን ባለሙያው አሰፋ መስፍን፤ በኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት እመርታዊ ለውጥና ማንሰራራት ማምጣቱን ገልጸው ለቀጣዩ እቅድ የላቀ ስኬት መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። በተለይም በአርተፊሻል ኢንተለጀንስና ሌሎች የቴክኖሎጂ ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶችን አንስተው በፋይናንስ ተቋማትና ሌሎች ተቋማት የታየውን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማሳያነት ጠቅሰዋል። በመሆኑም የዲጂታል ልማት ስትራቴጂ ለፍጥነት፣ ፈጠራና ለሀገር እድገት ወሳኝ በመሆኑ ለ2030 ስትራቴጂክ እቅድ ስኬት ሁላችንም የድርሻችንን መወጣት አለብን ብለዋል።