ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
በክልሉ የሚገኙ የቴክኒክ እና ሙያ ተቋማት በቴክኖሎጂ የታገዘ የመማር ማስተማር ስራ ላይ ማተኮር ይጠበቅባቸዋል -ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን
Jan 15, 2026 153
አሶሳ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሚገኙ የቴክኒክ እና ሙያ ተቋማት በቴክኖሎጂ የታገዘ የመማር ማስተማር ስራ ላይ ማተኮር እንዳለባቸው የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን ገለጹ። የአሶሳ ግብርና ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኮሌጅ ከ70 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባው የተሻሻለ የመስኖ አውታር ቴክኖሎጂ ተመርቆ ወደ ስራ ገብቷል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን በወቅቱ እንደተናገሩት፤ የቴክኒክ እና ሙያ ተቋማት በቴክኖሎጂ የታገዘ የመማር ማስተማር ስራ በማከናወን ስራ ፈጣሪ ዜጎችን ማፍራት ላይ ማተኮር አለባቸው። የአሶሳ ግብርና ኮሌጅም በሰለጠኑበት ሙያ ብቁ የሆኑ ሰልጣኞችን ለማፍራት የጀመረውን ጥረት ማጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል። ከዚህም በተጨማሪ ኮሌጁ ዘመናዊ የግብርና መካናይዜሽንን በማስፋት አርሶአደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ እያከናወናቸው የሚገኙ የምርምር ስራዎች መቀጠል እንዳለባቸው ተናግረዋል። ኮሌጁ የሚያፈልቃቸው አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችም የኮሌጁን መማር ማስተማር ስራ ከማገዝ በተጨማሪ ለአርሶአደሩ ተሞክሮ እንደሚሆኑም ገልጸዋል። የአሶሳ ግብርና ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኮሌጅ ዲን አቶ ሙስጠፋ ያሲን በበኩላቸው፤ ኮሌጁ የግብርናውን ዘርፍ የሚደግፉ የሰለጠኑ ባለሙያዎችን ለማፍራት አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እያስተዋወቀ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ ወደ ስራ የገባው የመስኖ አውታር የተለያዩ አትክልቶችን በማልማት ለመማር ማስተማር እና ለቴክኖሎጂ ሽግግር የሚያግዝ መሆኑን አንስተዋል። በምርቃት ስነ-ስርዓቱ ላይ የተገኙት የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የኮሌጁን የሥራ እንቅስቃሴ ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ ትግበራ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትና የሀገርን እድገት መሰረት ያደረገ ነው
Jan 15, 2026 108
መቀሌ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ ትግበራ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትና የሀገርን እድገት መሰረት ያደረገ መሆኑን የዘርፉ ምሁራን ገለጹ። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በስኬት ተጠናቆ በሚቀጥሉት አምስት አመታት የሚተገበር ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በቅርቡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ይፋ መደረጉ ይታወቃል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በዲጂታል አገልግሎት መሰረታዊ የሚባል ለውጥና ተጨባጭ የሚባሉ ውጤቶች የተመዘገቡበት ለመሆኑ በርካታ ማሳያዎችን ማንሳት ይቻላል። በዚህ ረገድ በተለይም በፋይናንስ አገልግሎቶች መሰረታዊ የሚባል የአሰራር ለውጥ በማምጣት አገልግሎታቸውን ይበልጥ በማሻሻል ላይ ሲሆኑ የቴሌ ብር እና ሌሎችም የዲጂታል አገልግሎቶች ሌላ እድል ይዘው መጥተዋል። በእነዚህና ሌሎች ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 እቅድ ትግበራ የላቀ ስኬት የተመዘገበበት በመሆኑ ከዚህ ተሞክሮ በመሰነቅ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የላቀ ስኬት ለማምጣት ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል። በአጠቃላይ በዲጂታል ልማት ትግበራና ቀጣይ እቅዶች ላይ ኢዜአ በትግራይ ክልል መቀሌ ከተማ ያነጋገራቸው የዘርፉ ባለሙያዎች የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ ትግበራ የዜጎችን ተጠቃሚነትና የሀገርን ሁለንተናዊ እድገት መሰረት ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የትግራይ ክልል ቅርንጫፍ የእርሻና ባዮ ቴክኖሎጂ ከፍተኛ ተማራማሪ እያሱ አብርሃ(ዶ/ር)፤ በዲጂታል እቅድና ተግባራዊ እንቅስቃሴ ኢትዮጵያ አስደናቂ ጉዞ ላይ መሆኗ በተግባር እየታየ ነው ብለዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ ከሚባለው በላይ ትልቅ ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን አንስተው የቀጣይ አምስት ዓመታት ስትራቴጂክ እቅድም በውጤታማነት የሚተገበር እንደሚሆን አመላክተዋል። የዲጂታል 2030 ስትራቴጂክ እቅድ ከገጠር እስከ ከተማ ሁሉን አቀፍ የህዝብ ተጠቃሚነት መሰረት ያደረገ መሆኑን ገልጸው በተለይም ለአርሶ አደሩ አጠቃላይ መረጃ፣ የምርት ገበያ ሁኔታ፣ የብድር አቅርቦትና አገልግሎቶችን በዲጅታል መጠቀም የሚያስችል ይሆናል ብለዋል። የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና ፍትሃዊ የግብርና ግብአትና ቴክኖሎጂን ተደራሽ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት የዲጂታል ትግበራው ከፍተኛ እገዛ የሚኖረው መሆኑንም አስረድተዋል። በድምሩ የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ ትግበራ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትና የሀገርን እድገት መሰረት ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የትግራይ ክልል ቅርንጫፍ አስተባበሪ አብርሃ ኪዳነማርያም (ዶ/ር)፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂክ ትግበራ የኤሌክትሪክ ኃይል እና የቴሌኮም ተደራሽነትን መሰረት ያደረገ በመሆኑ በገጠርም ይሁን በከተማ የዜጎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ መሆኑን አንስተዋል። የእቅዱ ትግበራ በተለይም በገጠር የአርሶ አደሩን ህይወት ቀለል የሚያደርግና እንግልትን የሚያስቀር በመሆኑ ልዩ ትርጉም ያለው በመሆኑ ለስኬቱ የሁሉም አካላት ትጋት ያስፈልጋል ብለዋል። የግብርና ሜካናይዜሽንን ለማሳካትና የአርሶ አደሩን የገንዘብ እንቅስቃሴ በማዘመን በቀላሉ የብድር አገልግሎትና የገበያ አማራጮችን እንዲያይም ትልቅ እድል መሆኑን አስረድተዋል። ለእቅዱ መሳካት የመንግስት ጥረት እንዳለ ሆኖ የግሉም ዘርፍ ጠንካራ ተሳትፎ አስፈላጊ መሆኑን ያነሱት ባለሙያዎቹ በትብብር የኢትዮጵያን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ማሳካት ይገባል ብለዋል።
በኦሮሚያ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በ27 ማዕከሎች ላይ እየተሰጠ ነው
Jan 15, 2026 73
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በ27 ማዕከሎች ላይ እየተሰጠ መሆኑን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ገለጸ። መንግስት በተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ በህዝቡ ይነሳ የነበረውን ቅሬታ ለመፍታት በርካታ ውጤታማ ስራዎች እያከናወነ ሲሆን ከእነዚህ መካከል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ይገኝበታል። በአዲስ አበባ ከተማ የተጀመረው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ወደ ክልሎችም ተስፋፍቶ የመሬት፣ የገቢ እና ሌሎች አገልግሎቶች በአንድ ማዕከል እየተሰጡ መሆኑ ይታወቃል። የኦሮሚያ ክልል ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ሃይሉ አዱኛ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ በክልሉ መንግስታዊ አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በክልሉ በሸገር፣ በአዳማ፣ በቢሾፍቱ፣ በጅማ እና በሻሸመኔ ከተሞች የተጀመረው አገልግሎቱ በዚህ ወቅት ወደ 27 ማዕከሎች ማስፋት መቻሉን ተናግረዋል። አገልግሎቱ በተለይም የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ከመመለስ እና ብልሹ አሰራሮችን ከማስቀረት ጋር በተገናኘ ህዝቡ ለረጅም ጊዜ ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት እያገዘ መሆኑን ገልጸዋል። ማዕከላቱ በርካታ አገልግሎቶችን በአንድ መስኮት መስጠት ማስቻሉ ብቻ ሳይሆን ተገልጋዩ በአጭር ጊዜ ጉዳዩን እንዲፈጽም እያስቻሉ ነው ብለዋል። በቀጣይም በተማ አስተዳደር ደረጃ ያሉትን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎቶች ወደ ክፍለ ከተሞች የማውረድ ስራ በትኩረት እንደሚከናወንም ተናግረዋል። በክልሉ በየደረጃው ያለው አመራርም ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር የተያያዙ ችግሮች እንዲቀረፉ ከሌሎች የልማት ስራዎች እኩል ትኩረት ሰጥቶ እየተረባረበ መሆኑን አስረድተዋል።
ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የሴቶችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ እና ተጠቃሚነት ለማሳደግ ያግዛል
Jan 14, 2026 152
ሰመራ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የሴቶችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንደሚያግዝ የአፋር ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ፋጡማ መሐመድ ተናገሩ። "ፋይዳ ለሴቶች" በሚል መሪ ሐሳብ በአፋር ክልል የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ የንቅናቄ መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ የተገኙት የአፋር ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ፋጡማ መሐመድ እንዳሉት፤ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ እና ተጠቃሚነት ለማሳደግ ያለው ሚና ከፍተኛ ነው። በተለይም ሴቶች በፋይናንሱ ዘርፍ እና በዲጂታል የአገልግሎት አሰጣጥ የሚኖራቸው ተሳትፎ እንዲያድግና ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያበረክተው አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል። ንቅናቄውን ተከትሎ እንደ አፋር ክልል በተያዘው ዓመት አንድ ሚሊዮን ሴቶች ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ እንዲኖራቸው እየተሰራ ነው ብለዋል። የንቅናቄ ስራው በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች እስከታች ድረስ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልፀው፤ በዚህ ረገድ ለተያዘው ዕቅድ ስኬታማነት የሀገር ሸማግሌዎችና የሃይማኖት አባቶች የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር ፅህፈት ቤት ኀላፊ አቶ አሚን መሐመድ በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በተለይም የሴቶችን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ነው። የዲጂታል መታወቂያ አገልግሎቱን በተቀላጠፈ ሁኔታ ተደራሽ ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም አመልክተዋል። ሴቶች ተደራጅተው የተለያዩ አገልግሎቶችን ለማግኘትም ሆነ በተለያዩ ሥራዎች ውስጥ በመሳተፍ ተጠቃሚ ለመሆን ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ያለው አበርክቶ ላቅ ያለ መሆኑንም አስረድተዋል። የተጀመረውን የንቅናቄ ተግባሩ እንዲጠናከር በማድረግ በክልል ደረጃ የተያዘው ዕቅድ እንዲሳካ በቁርጠኝነት ይሰራል ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ ከሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ነዋሪዎች፣ ከተለያዩ ማህበራት፣ ከሴቶች አዳሪ ትምህርት ቤትና ከሰመራ ዩኒቨርሲቲ የመጡ ሴቶች ተገኝተው ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያውን ለማግኘት ተመዝግበዋል።
ከምርምር ማዕከሉ የሚወጡ የስንዴ ዝርያዎች የአርሶ አደሮችን ምርታማነት አሳድገዋል
Jan 14, 2026 170
ሮቤ ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ ከሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል ያገኟቸው የተሻሻሉ የስንዴ ዝርያዎች ምርታማነታቸውን በማሳደግ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው በባሌ ዞን የሲናና ወረዳ አርሶ አደሮች ተናገሩ። የምርምር ማዕከሉ በበኩሉ የአርሶና አርብቶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ በምርምር ያገኛቸውን የሰብል ዝርያዎች በማባዛት ተደራሽ ለማድርግ እየሰራ መሆኑን ገልጿል። ከሲናና ወረዳ አርሶ አደሮች መካከል አቶ አወል ሀጅ ኢድሪስ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ከዚህ በፊት የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በአግባቡ ተግባራዊ ባለማድረጋቸው ተጠቃሚ ሳይሆኑ ቆይተዋል። ሆኖም ዓምና ከሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል ያገኙትን "ሳነቴ" የተሰኘ የስንዴ ዝርያ በአንድ ሄክታር ማሳቸው ላይ በማልማት 55 ኩንታል ምርት በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። ያገኙት ምርት ቀደም ሲል ከሚዘሩት የአካባቢ ዝርያ ጋር ሲነፃፀር በ30 ኩንታል ብልጫ ማሳየቱን አስረድተዋል። ምርታማነታቸውን ይበልጥ ለማሳደግ በ2017/018 የመኸር ወቅት የተሻሻሉ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ በአንድ ሄክታር ይዞታቸው ላይ ካለሙት ''ቦኩ'' ከተሰኘ አዲስ የስንዴ ዝርያ 65 ኩንታል ምርት እንደሚጠብቁ አስረድተዋል። ከምርምር ማዕከሉ ያገኙትን የስንዴ ዝርያ ሙሉ ፓኬጅ በመጠቀም ከ14 አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በኩታ ገጠም 25 ሄክታር መሬት ማልማታቸውን የገለጹት ደግሞ ሌላኛው የወረዳው አርሶ አደር ታጁ አብዱልቃድር ናቸው። በአሁኑ ወቅት የሰብሉ ቁመና በመልካም ሁኔታ ላይ ስለሚገኝ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁም ተናግረዋል። አርሶ አደር ከድር ሐጅ መሐመድ በበኩላቸው፤ ከዚህ በፊት ሰብልን በወቅቱ በማረምና ፀረ አረም በመርጨት ረገድ ክፍተት ስለነበረባቸው የልፋታቸውን ያህል ምርት ሳያገኙ ቆይተዋል። የሻይ ልማትን ለማላቅ እየታተረች ያለችው ኢትዮጵያ የማዕከሉ ተመራማሪዎች የሰጧቸውን የኤክስቴንሽን ምክር ሀሳብ በአግባቡ ተግባራዊ በማድረግ ከዘሩት የስንዴ ሰብል ከሄክታር እስከ 50 ኩንታል ምርት አገኛለሁ ብለው እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል ዋና ዳይሬክተር አቶ ታመነ ሚደቅሳ እንደገለጹት፣ ማዕከሉ የአርሶና አርብቶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን በምርምር በማፍለቅ ተደራሽ ለማድረግ እየሰራ ይገኛል። በተለይ ማእከሉ ለአካባቢው አርሶ አደሮች በቅርበት በምርምር የተደገፈ እገዛ በማድረግ ምርትና ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ እገዛ ማድረጉን አስረድተዋል። ይህን ተግባር በማጠናከርም በ2017/2018 ምርት ዘመን ብቻ ከማዕከሉ የተለቀቁ የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ ከ150 ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የቅድመ መሥራች ዝርያዎችን እያባዛ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በ1978 ዓ.ም የተቋቋመው የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል በስንዴ፣ ገብስና ሌሎች ስምንት መስኮች ላይ ያተኮሩ ምርምሮችን በማካሄድ ከ116 በላይ የምርምር ውጤቶችን ለተጠቃሚው ማድረስ መቻሉም ተመልክቷል።
የዲጂታል ስትራቴጂ ትግበራ በዘርፉ ልማት ኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርግ ነው
Jan 14, 2026 622
አርባ ምንጭ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የዲጂታል ስትራቴጂ ትግበራ በዘርፉ ልማት ሀገሪቷን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርግ መሆኑን በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉ ምሁራን ገለጹ። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 የተገኘውን ስኬት በመሰነቅ በዘርፉ ልማት የላቀ ስኬት ለማስመዝገብ የሚያስችል የቀጣይ አምስት ዓመታት ስትራቴጂክ ፕላን ይፋ መደረጉ ይታወቃል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂክ ዕቅድ የኤሌክትሪክ ኃይል እና የኢንተርኔት አገልግሎትን በማስፋት በተደመረ አቅም ለማሳካት የሚያስችል ዝግጅት በማድረግም ወደ ስራ ተገብቷል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት መረጋገጥ የላቀ ሚና ይጫወታል በዘመናዊ ዓለም ሁለንተናዊ ተወዳዳሪ ለመሆን ከምንም በላይ የዲጂታል ልማትና የቴክኖሎጂ አቅምን ማሳደግ መሰረታዊ ጉዳይ በመሆኑ መንግስት ለዘርፉ ትኩረት ሰጥቶ በመስራት ላይ መሆኑም ይታወቃል። በመሆኑም የዘርፉን ዕቅድና ትግበራ በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉ ምሁራን፤ የኢትዮጵያ የዲጂታል ስትራቴጂ ትግበራ በዘርፉ ልማት ሀገሪቷን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው ኮምፒዩቲንግና ሶፍትዌር ምህንድስና ፋካልቲ ዲን ጌታሁን ትዕግስቱ (ረዳት ፕሮፌሰር) የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በዘርፉ ልማት ጥሩ መሰረት ያኖረ ስለመሆኑ አስታውሰዋል። ከዚህ ስኬት በመነሳትም የ2030 ስትራቴጂክ ዕቅድ ትግበራ በይፋ መጀመሩ ኢትዮጵያን በዲጂታል አገልግሎት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርጋት መሆኑን ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የኮምፒዩቲንግና ሶፍት ዌር መምህር ተመራማሪ እና የዲጂታል ትምህርት ክፍል ዳይሬክተር መሐመድ አበበ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የምትከተለው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ስርአት በቴክኖሎጂ እንዲደገፍ የዲጂታል አሰራር ምቹ መደላድል እየፈጠረ ነው፡፡ መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት ዜጎች በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዘመኑን የዋጀ የቴክኖሎጂ ዕውቀት እንዲጨብጡና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፣ ዲጂታል አሰራሩ ዜጎች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ እንዲሆኑና ወጥ የሆነ መረጃ እንዲኖራቸው ማስቻሉን ገልጸዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ኢትዮጵያን ካደጉ ሀገራት ጋር በዘርፉ ያላትን ተወዳዳሪነት የሚያሳድግ ብሎም የቴክኖሎጂ ማዕከል እንድትሆን የሚያስችል ነው። በተለይ በኤሌክትሪክና ኔትዎርክ መሠረተ ልማት ማስፋፋት ላይ ትኩረት መደረጉ ዜጎች በፍትሃዊ መንገድ ዲጂታል አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያደርግ መሆኑን አስረድተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ታህሳስ 11 ቀን 2018 ዓ.ም በይፋ ማስጀመራቸው የሚታወስ ነው። በወቅቱም ስትራቴጂው ተደራሽነትን ማስፋት፣ እኩል ዕድል ማመቻቸት እና በተቋማትና ህዝብ መካከል መተማመንን መፍጠር ላይ ያተኮሩ ትልሞች እንዳሉት ማብራራታቸውም እንዲሁ።
የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ያካተቱ የተሽከርካሪ ታርጋዎችን ሥራ ላይ ሊያውል ነው
Jan 13, 2026 155
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አሁን እየተጠቀመበት ያለውን የተሽከርካሪ ታርጋ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ባካተተ አዲስ ታርጋ ሊቀይር መሆኑን የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አዛዥ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል አስታወቁ። የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወር የዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ አካሂዷል። የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አዛዥ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል እንደተናገሩት ፖሊስ አሁን እየተጠቀመባቸው ያሉ የተሽከርካሪ ታርጋዎችን ሙሉ በሙሉ በመቀየር አዳዲስና ዘመናዊ ታርጋዎችን በቅርቡ ስራ ላይ ለማዋል ዝግጅት ማጠናቀቁን ተናግረዋል። ይህም ተቋሙ የወንጀል መከላከልና ምርመራ ስራውን በዘመናዊ መንገድ ለመምራት ከጀመራቸው የሪፎርም ስራዎች አንዱ መሆኑን ተናግረዋል። አዲሱ ታርጋ የረቀቁ የቴክኖሎጂ ቁልፎች ያሉት ሲሆን የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስን ብቻ የሚወክል፣ የተቋሙን የሙያ ብቃት እንዲሁም የዲሲፕሊን ደረጃ የሚያንፀባርቅ መሆኑን ገልጸዋል። ኮሚሽነር ጀነራሉ አዲሱ ታርጋ ታትሞ በሚቀጥሉት ጥቂት ሳምንታት ውስጥ በይፋ ጥቅም ላይ እንደሚውል አረጋግጠዋል።
ኢትዮጵያን በአቪዬሽን ዘርፍ ተወዳዳሪ ማድረግ የሚያስችል አቅም እየተገነባ ነው - ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ(ዶ/ር)
Jan 13, 2026 126
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያን በአቪዬሽን ዘርፍ ተወዳዳሪ ማድረግ የሚያስችል አቅም እየተገነባ መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ(ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን ለሁለት ተቋማት የስራ ፈቃድ ሰጥቷል። የስራ ፈቃዱ የተሰጠው በአውሮፕላን ጥገና ዘርፍ በኢትዮጵያ አየር ሃይል ውስጥ ለተቋቋመው እና ለግል አየር መንገዶች ጥገና ለሚሰጠው ተቋም ነው። ባለስልጣኑ በተመሳሳይ ለዓለም አቀፍ የካርጎ አቪዬሽን አገልግሎት ደግሞ የአቪዬሽን ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት የስራ ፈቃድ ሰጥቷል። የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያን የበረራ ትራንስፖርት (አቪዬሽን) ማዕከል ለማድረግ የተለያዩ የለውጥ እርምጃዎች እየተወሰዱ ነው፡፡ በዚህም በዘርፉ የኢትዮጵያን ተወዳዳሪነት የሚያሳድግ አቅም እየተገነባ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ግንባታውን በይፋ ያስጀመሩት የቢሾፍቱ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል፡። በዛሬው ዕለትም ለሁለቱ ተቋማት የተሰጠው የስራ ፈቃድ በአቪዬሽን ኢንዱስትሪው ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን አንስተዋል፡፡ ለኢትዮጵያ አየር ሃይል በጥገና ዘርፍ የተሰጠው የስራ ፈቃድ የግል አየር መንገዶች ለአውሮፕላን ጥገና የሚያወጡትን ወጪ በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በተመሳሳይ የዓለም አቀፍ ካርጎ አቪዬሽን አገልግሎት የአቪዬሽን ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት ፈቃድ ማግኘቱ በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ሃይል ለማፍራት በሚደረገው ሀገራዊ ጉዞ ትርጉም ያለው ሚና እንደሚኖረው አስታውቀዋል። ማሰልጠኛው ከኢትዮጵያ አልፎ በአህጉር ደረጃ ባለሙያዎችን ለማፍራት ለሚደረገው እንቅስቃሴ አዎንታዊ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ዮሃንስ አበራ በበኩላቸው፤ ለተቋማቱ እውቅና የተሰጠው አስፈላጊውን መስፈርት ማሟላታቸው ተረጋግጦ መሆኑን ተናግረዋል። በስነ-ስርዓቱ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ(ዶ/ር)፣ የኢፌዴሪ የአየር ሃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳን ጨምሮ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል፡፡
የተቋሙ የዘመናዊነት ጅማሮና ዲጂታል ኢትዮጵያ ይዞት የመጣው ዕድል
Jan 13, 2026 116
ኢትዮጵያ ዘመናዊነት መላበስ በጀመረችበት ወቅት ለህዝብ አገልግሎት እንዲሰጡ ከተቋቋሙ ቀደምት ተቋማት መካከል አንዱ ነው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት፡፡ አገልግሎቱ አሰራሩን ሊያቀላጥፉ የሚችሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀምና የደንበኞችን እርካታ መጨመር ባለመቻሉ በተደጋጋሚ ቅሬታ ሲያስተናግድ ቆይቷል። በለውጡ ዓመታት በኢትዮጵያ ዘመናዊ፣ ዘመን ተሻጋሪና ጠንካራ የመንግሥት የአገልግሎት ሥርዓት መዘርጋት የሚያስችል ሪፎርም መካሄዱ ይታወቃል። የመንግስት አገልግሎቶችን በቴክኖሎጂ በማዘመን ፈጣን፣ ቀልጣፋ እና ከብልሹ አሰራር ለማጽዳት የተጀመረው ጥረት ሕብረተሰቡ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ እርካታ እንዲኖረው እያደረገ ይገኛል። ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ኤሌክትሪክ ወሳኝ እንደመሆኑ አገልግሎቱ ለዚህ አስቻይ ሁኔታን ሊፈጥሩ የሚችሉ አሰራሮችን መተግበር ግድ ይለዋል። አገልግሎቱ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የኤሌክትሪክ ሽፋንን ለማሳደግ የጀመራቸው ሥራዎች ውጤታማ እየሆኑ ይገኛሉ። ነገር ግን ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት የተያዘው ግብ እውን እንዲሆን ተቋሙን ማዘመን ወሳኝ ጉዳይ ነው። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አሥፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ አሁን ካለው ዓለም አቀፋዊ ነባራዊ ሁኔታ አንጻር አሰራርን ከማዘመንና ቴክኖሎጂን ከመጠቀም ውጪ በቀደመው አሰራር ሀገርን ማሻገር አይቻልም ብለዋል። ይህን ተከትሎ አገልግሎቱ አሰራሩን በቴክኖሎጂ የታገዘ ማድረግ፣ ልምድ ካላቸው ተቋማት ጋር በጋራ መስራት እንዲሁም የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማቶችን ለቴክኖሎጂ ምቹ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የተያዙ ግቦች እውን እንዲሆኑ ከፍተኛ እገዛ እንዳለው ነው ያስረዱት። ዋና ሥራ አሥፈጻሚው እንደሚሉት ተቋማቸው ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂ በመጠቀም የደንበኞችን እርካታ የሚጨምሩ አሰራሮችን ተግባራዊ ማድረግ ጀምሯል። ለአብነት የደንበኞችን እንግልት ለመቀነስና ተገልጋዮች ባሉበት ሆነው የአገልግሎት ክፍያቸውን የሚፈጽሙበት አሰራር ተግባራዊ ማድረጉን ገልጸዋል። አገልግሎቱ ከመልካም አስተዳደርና ከሙስና ጋር ተያይዞ ተደጋጋሚ ቅሬታ ሲነሳበት እንደነበር አስታውሰውም የጥቆማ አቀባበሉን በማዘመን ለቅሬታዎች ፈጣን ምላሽ መስጠት ተጀምሯል ብለዋል። ተቋሙ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ወስጥ ዘመናዊና የደንበኞችን ፍላጎት የሚያረካ እንዲሆን የጀመራቸውን ሥራዎች የበለጠ እንደሚያጠናክርም አረጋግጠዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂክ እቅድ የሀገርን እድገትና ማንሰራራት እውን ለማድረግ ወሳኝ ነው
Jan 13, 2026 99
አሶሳ፤ ጥር 5/2018 (ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂክ እቅድ የሀገርን እድገትና ማንሰራራት እውን ለማድረግ ወሳኝ የልማት ዘርፍ መሆኑን የዘርፉ ምሁር ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ይፋ ሲያደርጉ በሰጡት ማብራሪያ ዲጂታል ኢትዮጵያ ፍትሐዊ እና አስተማማኝ እንዲሁም ትክክለኛ መረጃን ተደራሽ ለማድረግ የሚያግዝ መሆኑን መግለፃቸው ይታወሳል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 የተገኘውን ስኬት በመሰነቅ በዘርፉ ልማት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር የሚያስችልና የሀገርን እድገትና ማንሰራራት የሚያረጋግጥ መሆኑ ይታመናል። በመሆኑም ስትራቴጂክ እቅዱን ለማሳካት ከመንግሥት ጥረት ባለፈ የግሉ ዘርፍና አጠቃላይ የዜጎች የተቀናጀ ጥረትና ተሳትፎ ወሳኝ ይሆናል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት እና በኢንፎርሜሽን እና ኮሚዩኒኬሽን ኢንጂነሪግ ተባባሪ ፕሮፌሰር መልካሙ ደሬሳ (ዶ/ር)፤ ለዲጂታል ልማት መንግስት የሰጠው ትኩረት የዓለምን ነባራዊ እውነታ በተገነዘበ መልኩ መሆኑን ገልጸዋል። የዲጂታል ቴክኖሎጂ ከዓለም ጋር ውድድር የሚገባበት በመሆኑ ለዘርፉ ትኩረት ሰጥቶ ከመስራት ውጭ አማራጭ የሌለ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም መሰረት ያለፉት አምሰት ዓመታት ትግበራ እና ቀጣይ የተያዘው አቅጣጫ በብዙ መልኩ የኢትዮጵያን ተወዳዳሪነት የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በዘርፉ ልማት ጥሩ መሰረት ያኖረ መሆኑን አንስተው የቀጣዩ ስትራቴጂክ እቅድ ደግሞ የላቀ ውጤት የሚመጣበት ስለመሆኑ አስረድተዋል። በቀጣይ የአርቲፊል ኢንተለጀንስ እና ሌሎች ዘመን አመጣሽ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በመጠቀምና በመወዳደር ለሀገር ልማትና እድገት መስራት ከሁላችንም ይጠበቃል ሲሉም አስገንዝበዋል። የንግድ ስርዓቱን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝ ማድረግም አስፈላጊ መሆኑን አንስተው የመሶብ አንድ ማእከልን ማስፋት፣ ፋይዳን ለሁሉም ዜጎች ተደራሽ ማድረግና የዲጅታል ግብይትን ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስኬት የሚወሰነው በሁሉም ጥረትና ትብብር ሲሆን በተለይም የኤሌክትሪክ ኃይል እና የኢንተርኔት አገልግሎትን ማስፋት ወሳኝ ይሆናል።
በአስተዳደሩ ተቋማት የሚሰጡትን አገልግሎት የሚያሳልጥ የቴክኖሎጂ አሰራር አቅም ተገንብቷል
Jan 12, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተቋማት የሚሰጡትን አገልግሎት የሚያሳልጥ የቴክኖሎጂ አሰራር አቅም መገንባቱን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ወንድሙ ሴታ ገለጹ። በአዲስ አበባ ከተማ 23 ወረዳዎች በኃይል መቆራረጥ የሚፈጠርን የአገልግሎት አሰጣጥ ክፍተት ምላሽ የሚሰጥ የፀሐይ ኃይል ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል። በዚሁ ጊዜ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ወንድሙ ሴታ፤ የመዲናዋን ነዋሪዎች የተቋማት የአገልግሎት ፍላጎት እርካታ የሚያረጋግጥ ዘመናዊ አሰራር እየተዘረጋ ነው ብለዋል። በዚህም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የፈጠረው ዘመናዊ የቴክኖሎጂ የአሰራር ሥርዓት አቅም ለተገልጋዮች የሚሰጡ አገልግሎቶችን በማሳለጥ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በወረዳዎች የተገነባው የፀሐይ ኃይል ፕሮጀክትም በኃይል መቆራረጥ ምክንያት የሚፈጠርን የአገልግሎት ክፍተት ምላሽ በመስጠት የደንበኛ እርካታን ለማረጋገጥ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተናግረዋል። በተለይም በወሳኝ ኩነት ምዝገባ ወቅት የኤሌክትሪክ ኃይል ሲቋረጥ ለሚፈጠሩ የአገልግሎት ክፍተቶች አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ለደንበኞች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እንደሚረዳ አስረድተዋል። በቀጣይም የከተማ አስተዳደሩ ተቋማት የሚሰጧቸውን አገልግሎቶች በአስተማማኝ የኃይል አቅርቦትና ዘመናዊ ቴክኖሎጂ አሰራር የማስቀጠል ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አንስተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ዮሴፍ ንጉሴ፤ የፀሐይ ኃይል ፕሮጀክቱ የወሳኝ ኩነት አገልግሎቶችን ለማሳለጥ ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብለዋል። በቀጣይም አገልግሎት በሚበዛባቸው ወረዳዎች የፀሐይ ኃይል ፕሮጀክቶችን በማስፋት አስተማማኝ የኃይል አቅርቦት እንዲያገኙ በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል። የቦሌ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈፃሚ እሸቱ ለማ (ዶ/ር)፤ የፀሐይ ኃይል ፕሮጀክቱ በኃይል መቆራረጥ ምክንያት የሚፈጥርን የአገልግሎት ክፍተት አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት እንደሚረዳ ተናግረዋል።
በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 የተከናወኑ ተግባራት ሀገር ወደተሻለ ከፍታ እንድታመራ መሰረት ጥለዋል
Jan 11, 2026 192
ወልቂጤ፤ ጥር 3/2018 (ኢዜአ)፡-በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የተከናወኑ ተግባራት ሀገሪቱ ወደተሻለ ከፍታ እንድታመራ መሰረት የጣሉ መሆናቸውን የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉ ምሁራን ገለጹ። ስትራቴጂው በቅርቡ ይፋ የተደረገውን ዲጂታል 2030 ትግበራን ለማሳካት ትልቅ ግብዓት እንደሚሆንም ምሁራኑ ጠቁመዋል። መንግስት የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ እውን ለማድረግ በየዘርፉ የጀመራቸውን ሥራዎች ይበልጥ ለማዘመንና ለማሳለጥ በቅርቡ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትግበራን ይፋ ማድረጉ ይታወሳል። ምሁራኑ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንዳሉት በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 የተተገበሩ ቴክኖሎጂዎች ሀገሪቱ ወደተሻለ ከፍታ እንድታመራ መሰረት የጣሉ ናቸው። ዲጂታል ቴክኖሎጂው በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርትና በፋይናንስ ዘርፎች ያመጣው ተጨባጭ ለውጥና ያስገኘው ጥቅም እያደገ መሆኑን የተናገሩት በዩኒቨርሲቲው የሶፍት ዌር ኢንጂነሪንግ መምህር በላይ አለምነህ ናቸው። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ስኬቶች በዘርፉ ልምድና ተሞክሮ የተቀሰመበት መሆኑን ገልጸው፣ በስትራቴጂው በተዘረጉ የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማቶች በተለያዩ ተቋማት ከወረቀት ነጻ የሆነ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን ተናግረዋል። በዩኒቨርሲቲውም የትምህርት መርሃ ግብሮችና በሥራ ክፍሎች የመረጃ ልውውጥ ሥራው ከወረቀት ነጻ በሆነ መንገድ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ታግዞ እየተከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ የትምህርት አሰጣጥ ሂደቱ በቴክኖሎጂ እንዲታገዝ በመደረጉ ተማሪዎች ጊዜና ቦታ ሳይገድባቸው ትምህርታቸውን በኦንላይን መከታተል መቻላቸውን ጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው ከተለያዩ ተቋማት እና ግለሰቦች ጋር የሚያደርገው ግንኙነትና የተማሪዎች ውጤትም በዲጂታል ቴክኖሎጂ ተደራሽ መደረጋቸውንም ነው ያመለከቱት። የመማር ማስተማር ሂደቱን በማዘመንና የፈተና አሰጣጥ ሥርአቱን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የፈተናን ደህንነት ለማስጠበቅ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም አስረድተዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የተከናወኑ ስኬታማ ተግባራት በቅርቡ ይፋ ለተደረገው ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትግበራ መሰረትና ግብአት መሆናቸውን ተናግረዋል። የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ኔትዎርኪንግ ሳይበር ደህንነት መምህር ወንድወሰን ዝና በበኩላቸው ለተማሪዎች በሳይበር መረጃ ደህንነት አጠባበቅ ላይ በተግባር የተደገፈ ትምህርት ለመስጠትና በቂ ዕውቀት ለማስጨበጥ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 አበርክቶ ላቅ ያለ መሆኑን ተናግረዋል። በየደረጃው ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት ይበልጥ መረጋገጥ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ገልጸው፣ "ይህን አጠናክሮ ለማስቀጠል በዲጂታል ቴክኖሎጂ ያሉ አማራጮችን በአግባቡ ልንጠቀምባቸው ይገባል" ብለዋል። ስትራቴጂው ዜጎች በዲጂታል ቴክኖሎጂ አማራጮች ታግዘው ባሉበት ቦታ ትምህርታቸውን መከታተል የሚችሉበት ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም ጠቁመዋል። እንደ መምህሩ ገለጻ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ተግባራዊ መሆን እንደሀገር ህገወጥ የገንዘብ ዝውውርን ከመከላከል ባለፈ የተለያዩ ማጭበርበሮችን ለማስቀረትም እያገዘ ነው። ዲጂታል 2030 ስትራቴጂ አካታችና ተደራሽ እንዲሆን በማድረግ በሁሉም ዘርፍ ተግባራትና የሚሰጡ አገልግሎቶች በቴክኖሎጂ የታገዙና ቀልጣፋ እንዲሆኑ የተጀመሩ ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸውም መምህሩ ገልጸዋል።
በከተማው ተሰጥኦ ያላቸውን ወጣቶች የዲጂታል እውቀት የማሳደግ ስራ ይከናወናል
Jan 11, 2026 156
ጎንደር ፤ጥር 3/2018(ኢዜአ)፡- በስራ ፈጠራ የሚሰማሩ ልዩ ተሰጥኦ ያላቸውን ወጣቶች የዲጂታል ቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት ለማጎልበት እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የጎንደር ከተማ አስተዳደር አስታወቀ። የጎንደር ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ እና "ኦርቢት ኢኖቬሽን ሀብ" የተባለ ድርጅት በጋራ በመሆን በስራ ፈጠራ ክህሎት ላሰለጠኗቸው 45 ወጣቶች ዛሬ የማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ሰጥተዋል። የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ወይዘሮ ደብሬ የኋላ ለሰልጣኞቹ እንደገለጹት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት ልዩ የስራ ፈጠራ ተሰጥኦ ያላቸውን ወጣቶች ተሳትፎ ማሳደግ ይገባል። የከተማ አስተዳደሩ ልዩ የስራ ፈጠራ ተሰጥኦ ያላቸውን ወጣቶች ተቋማዊ የአሰራር ስርአቶችን በመዘርጋት ውጤታማና እንዲሆኑ ሁለተናዊ ድጋፍ በማድረግ ሃላፊነቱን እየተወጣ ይገኛል ብለዋል፡፡ የዲጂታል ቴክኖሎጂ በሀገራችን ለተዘመገቡ ኢኮኖሚያዊ እድገቶች አዎንታዊ ሚና እንደነበረው ጠቁመው የሰራ ፈጠራ ሃሳብ ያላቸውን ወጣቶች በከተማው በማደራጀት ተሰጥዋቸውን ለሀገር ልማትና እድገት የሚያውሉበት ምቹ አውድ እንደሚፈጥር ገልጸዋል፡፡ የጎንደር ከተማ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዋና ዲን አቶ ተስፋሁን መኮንን እንደገለጹት የስራ ፈጠራ ሃሳብ ያላቸው ወጣቶች የዲጂታል ክህሎትና እውቀታቸው እንዲዳብር ኮሌጁ ተገቢውን የሙያ ስልጠና እንዲያገኙ እያደረገ ይገኛል፡፡ የስራ ፈጠራ ሃሳብ ተወዳዳሪነትን፣ ብቃትንና ዘመኑን የዋጀ መሆን እንዳለበት ጠቁመው ለስልጠናው የተመረጡ ወጣቶችም መስፈርቱን ያሟሉ እንደሆኑም ገልጸዋል፡፡ "የኦርቢት ኢኖቬሽን ሀብ" የኮሚኒቲ ዴቨሎፕመንት ፕሮግራም ማኔጀር ቅኔል ሃይሉ በበኩላቸው በሀገሪቱ በተለያዩ ክልሎች የስራ ፈጣሪ ወጣቶችን ራእይ ለማሳካት የዲጂታል ክህሎት ስልጠና የሚያገኙበት አሰራርን በመዘርጋት አየተተገበረ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ድርጅቱ ከቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ጋር በመተባበር በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በትግራይና በደቡብ ክልሎቸ በ6 ዙር የስራ ፈጠራ ሃሳብ ያላቸውን ወጣቶች በማወዳደር የቴክኖሎጂ ስልጠና እንዲያገኙ እየደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በጎንደር ከተማም 218 የስራ ፈጠራ ሃሳብ ያላቸውን ወጣቶች በማወዳደር ከዚህ ውስጥ መመዘኛውን ያለፉ 45 ወጣቶች ለሶስት ተከታታይ ወራት የንድፈ ሃሳብና የተግባር ስልጠና በመስጠት ወደ ስራ የሚገቡበትን ሁኔታ ማመቻቸቱን አስረድተዋል፡፡ ከሰልጣኞቹ መካከል የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ባልደረባ የሆኑት ዶክተር አዲሱ ወርቄ ስልጠናው በዲጂታል አለም ውስጥ የስራ ፈጠራ ሃሳቦቻችንን አንዴት ማሳካት እንደምንችል እውቀትና ክህሎት መጨበጥ እንድንችል አግዞናል ብለዋል፡፡ የሳይካትሪስት ባለሙያ የሆነችው ቤተልሄም ጌታቸው በበኩሏ የስራ ፈጠራ ሃሳቦቼን እንዴት ወደ መሬት ማውረድና ገበያ ላይ ማውጣት አንደምችል ስልጠናው የተሟላ እውቀትና ግንዛቤ ፈጥሮልኛል ብላለች። በስነ ስርአቱ ላይ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችን ጨምሮ ስልጠናውን የተከታተሉ ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ተሳታፊ ናቸው፡፡
የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዲጂታላይዝ የሆነ አሰራሩን ማጠናከር ይገባዋል
Jan 10, 2026 185
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የሪፎርም ስራዎችን በመተግበር አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረግ የሚያከናውናቸውን ተግባራት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስገነዘበ። የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ፣ ምክትል ሰብሳቢዎች እና ከምክር ቤቱ ሴቶች ኮከስ አመራር አባላት ጋር ውይይት አካሂዷል። ውይይቱም የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን እያከናወናቸው በሚገኙ የሪፎርም እና የዲጂታል ስራዎች፣ የግዥና ንብረት የህግ ማዕቀፎች እንዲሁም ወደፊት በትኩረት ሊሰራባቸው በታቀዱ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነው። የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ ፤ ባለስልጣኑ ሪፎርም ስራዎችን በመተግበር አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረግ የሚያከናውናቸውን ተግባራት ማጠናከር እንዳለበት ተናግረዋል። ባለስልጣኑ በተቋማዊ አቅም ግንባታ፣ በመንግስት ግዥና ንብረት ዲጂታላይዜሽን፣ ከዘለቄታዊነት የግዥና ንብረት አስተዳደር ሥርዓት በማጎልበት ከመንግስት ግዥና ንብረት አገልግሎት እና መረጃ ጥራትና ሽፋን ለማሳደግ ያከናወነው ስራ ለሌሎችም ተቋማት በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን ገልጸዋል። ተቋሙ እየተገበረ በሚገኘው ዘመናዊ አሰራር ከሀገር አልፎ ለሌሎች ሀገራትም ልምድ እያካፈለ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በመንግስት ግዥ ውጤታማ እንዲሆንና ግልጸኝነት ያለው አገልግሎት እንዲሳለጥ በማድረግ በኩል እያከናወነ ያለውን ተግባር ሊያጠናክር እንደሚገባ ገልጸዋል። የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር መሰረት መስቀሌ በበኩላቸው፤ ተቋሙ በዘመናዊ አሰራር በመታገዝ የግዥ ስርዓቱን ለማዘመንና የቁጥጥር ስርዓቱን ከማጠናከር አኳያ በርካታ ስራዎች እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ከግዥ ጋር ተያይዞ ያለውን ግልጸኝነት ከማረጋገጥ እና ህገ-ወጥነት ለመከላከል የሚያስችሉ የተለያዩ ዘመናዊ ስርዓቶችን መዘርጋቱን አብራርተዋል። ባለስልጣኑ የአሰራር ስርዓቱን ጥራትና ቅልጥፍና ለማሳደግ አዋጁን፣ መመሪያዎችንና የአሰራር ስርዓቶችን ተግባራዊ በማድረጉ አመርቂ ውጤት መመዝገቡን ጠቁመዋል። ለተገልጋዮች እና ለባለድርሻ አካላት ተከታታይ ሥልጠና መስጠቱንም ገልጸዋል። በተለይ የመንግስት ኤሌክትሮኒክ ግዥን (e-GP) ከፌዴራል ተቋማት አልፎ ወደ ክልሎች እና ከተማ አስተዳደሮች የማውረድ ስራዎች ማከናወኑን ጠቁመዋል። በውይይት የተሳተፉና አስተያየታቸውን የሰጡት የተለያዩ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዎች በበኩላቸው፤ ተቋሙ አሰራሩን ዘመናዊ እና ግልጸኝነት በማስፈን እያከናወነ ያለው ተግባር የሚበረታታ መሆኑን ተናግረዋል። በምክር ቤቱ የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ እንደገለጹት፤ ተቋሙ አሰራሩን ዲጂታላይዝ ለማድረግ የሚያከናውናቸው ተግባራት የሚበረታቱ ናቸው። የመንግስት ወጪ፣ አስተዳደር እና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሺመቤት ደምሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የመንግስት ግዥ ስርዓት ግልጽና ፍትሃዊ እንዲሆን እየተደረገ ያለው የመቆጣጠር ስራ የሚበረታታ መሆኑን ነው የገለጹት። ተቋሙ ከራሱ አልፎ ሌሎች ተቋማትን በዘመናዊ አሰራር ለማዘመን እያደረገ ያለው ተግባር የሚበረታታ መሆኑን ጠቁመዋል። የመንግስት ልማት ድርጅት ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ መለሰ መና በበኩላቸው፤ ባለስልጣኑ ቀልጣፋና ተደራሽ የሆነ አገልግሎት ለመስጠት ያደረገው ጥረት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ገልጸዋል። የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እጸገነት መንግስቱ በበኩላቸው፤ ባለስልጣኑ በምክር ቤቱ የወጡ አዋጆችን በአግባቡ በመተግበር ለሌሎችም ተቋማት ምሳሌ መሆኑን ገልጸዋል። ባለስልጣኑ የጀመረውን ተግባር በማጠናከር ለወደፊት የላቁ ስራዎችን ማከናወን እንደሚገባው አሳስበዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ለጉምሩክ አገልግሎት መቀላጠፍ ትልቅ ዕድል ይዞ መጥቷል
Jan 8, 2026 283
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018(ኢዜአ)፦ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ቀልጣፋ የጉምሩክ አገልግሎትን ለማጠናከር ትልቅ ዕድል ይዞ መምጣቱን የጉምሩክ ኮሚሽን አስታወቀ። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በስኬት መጠናቀቁን ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በይፋ ማስጀመራቸው ይታወቃል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል ዕድል መፍጠር እንዲሁም በዜጎችና በተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት ዋነኛ ዓላማዎቹ ናቸው። የጉምሩክ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሙሉ ወርቅ ደረሰ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ኮሚሽኑ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ ወቅት የንግድ እንቅስቃሴን የሚያሳልጡ፣ ኮንትሮባንድን ለመቆጣጠር የሚያስችሉና በአጠቃላይ የኮሚሽኑን ስራዎች የሚያሻሽሉ ቴክኖሎጂዎች ወደ ሥራ አስገብቷል። ቴክኖሎጂዎቹ ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ምርቶችን ክትትል ለማጠናከር፣ የሰው ንክኪና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል እንዲሁም ደንበኞች ባሉበት ሆነው አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችሉ ናቸው ብለዋል። በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የሚተገበረው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ደግሞ በጉምሩክ ዘርፍ የሚሰጡ አገልግሎቶችን ለማዘመን እና ለማቀላጠፍ ትልቅ እድል ይዞ መምጣቱን ጠቅሰዋል። ስትራቴጂውን ስኬታማ ለማድረግ የተቋማት ቅንጅት እንደ ዋነኛ የድጋፍ ማዕቀፍ መሆኑን በማንሳት፥ ኮሚሽኑ የበከሉን ይወጣል ብለዋል። በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዘ አሰራር ተግባራዊ መደረጉን ገልጸው፤ በሂደት ላይም ያሉ ቴክኖሎጂዎች በቀጣይ ወደ ስራ ይገባሉ ብለዋል። ምክትል ኮሚሽነሯ እንደገለጹት በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የጉምሩክ አገልግሎትን በቴክኖሎጂ የተደገፈ የማድረግ ሰራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ።
የኢትዮጵያ ሳተላይቶች ያመነጯቸው መረጃዎች ጉልህ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ አበርክተዋል
Jan 8, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሳተላይቶች ያመነጯቸው መረጃዎች ጉልህ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማበርከታቸውን የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ጂኦ ስፓሻል ኢንስቲትዩት ገለጸ። በሚቀጥለው ዓመትም ሶስተኛዋን የመሬት ምልከታ የመረጃ ሳተላይት ወደ ሕዋ ለማምጠቅ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል። የኢትዮጵያ የመጀመሪያዋን ሳተላይት ኢቲ-አር.ኤስ.ኤስ1 (ET-RSS1) እንዲሁም ሁለተኛው ኢቲ-ስማርት-አር.ኤስ.ኤስ (ET-SMART-RSS) የተሰኙ ሁለት የመረጃ ሳተላይቶችን ወደ ሕዋ ማምጠቋ ይታወሳል። የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ጂኦ ስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ቀደም ሲል ወደሕዋ የተላኩ ሁለት የመሬት ምልከታ ሳተላይቶች የአገልግሎት ጊዜያቸውን አጠናቀዋል። የመሬት ምልከታ የመረጃ ሳተላይቶቹም በርካታ ቴክኖሎጂያዊና ሳይንሳዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን ማበርከታቸውን ተናግረዋል። በዚህም የምግብ ዋስትና፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በተፈጥሮ ሃብት አያያዝ የግብርና መስኮች፣ በከተማ ፕላንና መሠረተ ልማት፣ በሀገር ሉዓላዊነትና ገጽታ ግንባታ ከፍተኛ ጠቀሜታ ማበርከታቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በሚቀጥለው ታኅሳስ 2019 ዓ.ም በምስል ጥራትና የጊዜ ቆይታ አቅም ያላት ኢቲ-አር.ኤስ.ኤስ 2 (ET-RSS2) የተሰኘች ሳተላይት ወደ ሕዋ ለማምጠቅ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። በቀጣይ የምትመጥቀው ኢቲ-አር.ኤስ.ኤስ 2 ሳተላይት ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመታጠቅ በሕዋ ላይ የአምስት ዓመታት የጊዜ ቆይታ እንዲኖራት ታሳቢ መደረጉ ነው የተገለጸው። ከዚህ ቀደም ወደ ሕዋ ከተላኩ ሳተላይቶች የተገኘውን መረጃ የመቀበል፣ የመተንተን፣ የመቆጣጠርና የጥገና አቅም መፈጠሩን አስረድተዋል። ሦስተኛዋን ሳተላይት ለማምጠቅ እየተደረገ የሚገኘው ጥረትም የኢትዮጵያን የሳተላይት ልማት አቅም በተግባር የሚያሳይ እንደሚሆን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ለሰው ሰራሽ አስተውሎት መሰረት እየጣለች ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jan 6, 2026 212
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የፖሊሲ ማዕቀፍ እና መሰረተ ልማትን ጨምሮ ለሰው ሰራሽ አስተውሎት መሰረት የሚጥሉ ስራዎችን እያከናወነች እንደምትገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን በማስመልከት በተዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ ጽሑፍ አቅርበዋል። በውይይት መድረኩ ላይ ከምሁራን ለቀረቡላቸው ጥያቄዎችም ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሰው ሰራሽ አስተውሎት (ኤ.አይ) በዓለም ደረጃ ያለው ተጽእኖ እና ድርሻ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል። በተጠናቀቀው የ2025 የፈረንጆቹ ዓመት ኤ.አይ በርካታ ስራዎችን መተካቱን አውስተው አሁንም በተጠናከረ መልኩ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። ፈጥነን ልጆቻችንን ካዘጋጀን ሰው ሰራሽ አስተውሎትን እንደ ተለያዩ ምርቶች በቀላሉ መጠቀም እንችላለን ብለዋል። ኤ.አይ ስራ ይቀማል ብዬ አልሰጋም ሲሉ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የሰው ልጅ መስራት የሰው ልጅ ሊሰራቸው የማይገባቸውን ስራዎች እየተካ ይሄዳል ነው ያሉት። ኤ.አይን የምንፈጥር እኛነን ኤ.አይን የምንቀይር እኛ ነን ቀድመን ግን ፋውንዴሽን መጣል ይገባናል ብለዋል። መንግስት ለሰው ሰራሽ አስተውሎት ፖሊሲ እና ስትራቴጂ አዘጋጅቶ እየተተገበረ መሆኑን ጠቅሰው ሳይንስ ሙዚየም አንዱ መሰረተ ልማት መሆኑን ተናግረዋል። መሰረተ ልማት እና ታለንት ለዘርፉ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱም ነው ያብራሩት። ኢትዮጵያ የምትገነባው የኤ.አይ ዩኒቨርሲቲም የኢትዮጵያን እና የአፍሪካን ብዙ ችግሮች ይፈታል ተብሎ እንደሚታመን ተናግረዋል። ዋናው ለልጆቻችን ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጆቻችን የሚወዳደሩበት ልጆቻችን ከሌላው አንስው የማይታዩበት ሁኔታ ለመፍጠርም እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ቀድሞ መወዳደር ቀድሞ መገኘት አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው ኤ.አይን በዛ መልክ ማየት እንደሚገባ ገልጸዋል። ኤ.አይ ስራዎችን በማቃለል እና ጊዜ በመቆጠብ ወሳኝ ድርሻ እንደሚወጡም ነው የገለጹት። ተማሪዎችም ኤ.አይን መጠቀም አለባቸው፤ ቴክኖሎጂዎቹን መጠየቅ እንዲችሉ አድርገን ከፈጠርናቸው ተማሪዎች ተወዳዳሪ መሆን እንደሚችሉ ገልጸዋል። የመጠየቅ ብቃት ችሎታ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚህ ረገድም ኤ.አይ የተማሪዎችን አቅም እንደሚገነባ ተናግረዋል። የመጀመሪያው ትውልድ ለኢኮኖሚ ቅድሚያ የሰጠ እና ሁለተኛው ትውልድ ፖለቲካዊውን ያስቀደመ መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአሁኑ ዘመን የሀሳብ ትውልድ እንደሆነም ጠቅሰዋል። ሀሳብ የሚወድ ትውልድ ችግሮች እየፈታ እና እያቀለለ እንደሚሄድም ተናግረዋል። ኤ.አይ ዝግጅት እና ስራ እንደሚፈልግ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ከመፍራት ይልቅ እውነታውን በመጋፈጥ ማሸነፍ እንችላለን ብለዋል።
ከተማርንና ዝግጁ ከሆንን በኤ አይ የማይናቅ ደረጃ ላይ እንደርሳለን-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jan 6, 2026 157
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 28/2018(ኢዜአ)፡- ከተማርንና ዝግጁ ከሆንን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሂደት የማይናቅ ደረጃ ላይ እንደርሳለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል በማስመልከት በተዘጋጀ የውይይት መድረክ ላይ ጽሑፍ አቅርበዋል። ጽሑፍ ካቀረቡ በኋላም ከምሁራን ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በዚሁ ወቅትም፤መንግሥት የኮሪደር ልማትና መንገድ ሠርቶ ለነዋሪው ሲያቀርብ ይህን በአግባቡ እንዴት መያዝ እንደሚቻል ደግሞ ምሁራን ከተሜነትን የሰው ልጅ ዐዕምሮ ላይ መሥራት ይጠበቅባችኋል ብለዋል። ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ጋር በተያያዘም ኢትዮጵያ ትልቅ ተስፋ ያላት ሀገር መሆኗን አንስተዋል። ኤ አይ ከሚፈልጋቸው ነገሮች አንዱ ኢነርጂ መሆኑን ጠቁመው፤ ከዚህ አንጻር ኢትዮጵያ ብዙ የማምረት ዐቅም እንዳላት አረጋግጠዋል። ኢነርጂ ላይ ኢንቨስት ካደረግን ለኤ አይ አንድ አስቻይ ጉዳይ ፈታን ማለት ነው ሲሉም ገልጸዋል። ሌላው ኤ አይ የሚፈልገው ጉዳይ መረጃ(ዳታ) እና የመረጃ ማዕከል(ዳታ ሴንተር) መሆኑንም አስገንዝበዋል። ከተማርን፣ ዝግጁ ከሆንን፣ እየሠራናቸው ያሉትንና በቀጣይ የምናከናውናቸውን ጨምሮ በመተባበር ለለውጥ ዝግጁ ሆነን በትጋት ከሠራን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሂደት የማይናቅ ደረጃ ላይ እንደርሳለን ብለዋል። ለኤ አይ ግብዓት የሚሆኑ ነገሮች በብዛት በአፍሪካ እንደሚገኙም አስገንዝበዋል።
ማዕከሉ በምርምር ያወጣቸውን የሰብል ዝርያዎችን ተደራሽ ለማድረግ የመነሻ ዘር ብዜት እያካሄደ ነው
Jan 5, 2026 199
ሮቤ፤ ታህሳስ 27/2018 (ኢዜአ)፦የሲናና ግብርና ምርምር መዕከል በምርምር ያገኛቸውን የተለያዩ የሰብል ዝርያዎች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ የመነሻ ዘር እያባዛ መሆኑን ገለጸ። ማዕከሉ አርሶ አደሮችና የባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ የመስክ ቀን ጉብኝት አካሂዷል። በመርሐግብሩ ላይ የተገኙት የምርምር ማዕከሉ ስራ አስኪያጅ አቶ ታመነ ሚደቅሳ እንዳሉት፤ማዕከሉ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በምርምር እየደገፈ ነው። በተለይ ማዕከሉ ባለፉት ዓመታት በስንዴ፣ ገብስና ሌሎች ስምንት የትኩረት መስኮች ላይ ተመስርቶ ምርምሮችን በማካሄድ 116 የምርምር ውጤቶችን ለተጠቃሚው ማድረሱን አስታውሰዋል። ማዕከሉ በቅርብ ጊዜ በምርምር ያወጣቸውን ዝርያዎች አርሶ አደሩ ጋር ተደራሽ እንዲሆኑ የመስራች ዘር የማባዛት ሥራ እያካሄደ መሆኑን ተናግረዋል። በሲናና አርሶ አደሮች በኩታገጠም አሰራር እየተባዛ ያሚገኘውና አርሶ አደሩ ልምድ እንዲለዋወጥ ዓላማ በማድረግ የተዘጋጀው የመስክ ምልከታ የዚሁ ጥረት አካል ነው ብለዋል። በማዕከሉ የግብርና ኤክስቴንሽን ተመራማሪ አቶ ባያታ ጋዲሳ በበኩላቸው፤ ማዕከሉ በምርምር የሚያወጣቸው የሰብል ዝርያዎች ውጤታማነታቸው ከተረጋገጠ በኋላ አርሶ አደሩ ጋር ተደራሽ እንደሚሆኑ አመልክተዋል። ዝርያዎቹ በስፋት ተጠቃሚው አርሶ አደር ጋር እንዲደርሱ በምርምር ማዕከሉና በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በማባዛት ተደራሽ እንደሚደረጉ አክሏል። አቶ ባያታ እንዳሉት፤ ማዕከሉ በአሁኑ የመኽር ወቅት በምዕራብ አርሲና በባሌ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች ከ150 ሄክታር በሚበልጡ የአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በቅርቡ ከማዕከሉ የተለቀቁ ዝርያዎችን እያባዛ መሆኑን አስረድተዋል። እየተባዙ ከሚገኙ ዝርያዎች መካከል በአንድ ሄክታር መሬት እስከ 72 ኩንታል ምርት የሚሰጥ ''ቦኩ'' የሚባል ስያሜ የተሰጠው የስንዴ ዝርያ እንደሚገኝበት አመልክተዋል፡፡ የመስክ ምልከታው ላይ የተሳተፉ አርሶ አደሮች በሰጡት አስተያየት፤ ማዕከሉ በአካባቢያቸው በመኖሩ የተሻለ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችን በየጊዜው በማግኘት ምርታማነታቸውና ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በ1978 ዓ.ም የተቋቋመው የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል እስከ አሁን 116 የሚሆኑ የሰብል፣ የእንስሳት መኖና ሌሎች የግብርና ቴክኖሎጂዎች ላይ ያተኮሩ ዝርያዎችን በምርምር በማፍለቅ ለተጠቃሚው ማሰራጨቱ ተገልጿል።