ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ዩኒቨርሲቲው በሚያከናውነው ግብርና ተኮር የምርምር ሥራዎች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ እያደረገ ነው
Apr 15, 2026 76
ጅማ ፤ ሚያዚያ 7/2018 (ኢዜአ)፦የሚያከናውናቸው ግብርና ተኮር የምርምር ሥራዎች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ እያደረጉ መሆኑን የጅማ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ። የጅማ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ስራው ጎን ለጎን ዘርፈ ብዙ የምርምር ሥራዎችን የሚያከናውን ሲሆን፣ ግብርና ተኮር የምርምር ሥራዎች ተጠቃሽ ናቸው። ዩኒቨርሲቲው በጅማ ዞን እና ሌሎች አካባቢዎች የሚገኙ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ለማድረግም የተፈጥሮ ማዳበሪያን አምርቶ ተደራሽ በማድረግ ላይ ይገኛል። የተፈጥሮ ማዳበሪያው በባዮቻር (Biochar) ላይ ተመስርቶ የተመረተ ሲሆን፣ የአፈር ጤንነትን በማሻሻል ምርታማነትን ከማሳደግ በተጨማሪ አካባቢን ከኬሚካል ተፅዕኖ ለመጠበቅ እንደሚያግዝም ተመልክቷል። 'ባዮቻር' የእርሻ ተረፈ ምርቶችና የቅጠላ ቅጠል ውጤቶችን በከፍተኛ ሙቀት በማቃጠል የሚገኝ የከሰል ዓይነት ሲሆን ይህም የከሰል ዓይነት የሚዘጋጅበት ዋነኛ ዓላማ ለማገዶነት ሳይሆን የአፈርን ለምነት ጠብቆ ለማቆየት ነው። በተጨማሪም የአፈር ለምነትን በማሻሻል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥ ችግሮችን ለመከላከል ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንም መረጃዎች ያሳያሉ ። በዩኒቨርሲቲው የግብርና እና እንስሳት ሕክምና ኮሌጅ ምክትል ዲን ፍቅረማርያም ገዳ (ዶ/ር)፤ ዩኒቨርሲቲው ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የምርምር ተግባራት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አስረድተዋል። አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ከሚያደርጉ የምርምር ስራዎች አንዱ በባዮቻር ላይ የተመሠረተ ማዳበሪያን ተደራሽ ማድረግ መሆኑን ገልጸው በእስካሁኑ ሂደትም ከ500 በላይ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያውን በአርሲ እና በባቱ ከሚገኙ የምርምር ማዕከላት ጋር በመሆን ለአርሶ አደሩ የማስፋፋት ሥራ እየተሠራ ሲሆን ፤ በተጨማሪም በሲዳማ ክልልም ተግባራዊ ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅት በጅማ ብቻ ከ300 በላይ አርሶ አደሮች የተፈጥሮ ማዳበሪያውን ከመጠቀም ባሻገር ሥልጠና ወስደው እራሳቸው በማምረት ላይ እንደሚገኙም ጠቁመዋል። ቡኖ በደሌ ዞንን ጨምሮ በአጎራባች ዞኖች ለባለሙያዎች እና ለአርሶ አደሮችም ሰፊ ሥልጠና እየተሰጠ መሆኑንም ተናግረዋል። በጅማ ዩኒቨርሲቲ ግብርና እና እንስሳት ሕክምና ኮሌጅ መምህርና ተመራማሪ ሚልኪያስ አህመድ (ዶ/ር) ለማዳበሪያው ዝግጅት አስፈላጊ የሆነው ባዮቻር አገልግሎት ላይ ካልዋሉ ተረፈ ምርቶች የሚዘጋጅ መሆኑን አመልክተዋል። የምርምር ሥራው ላለፉት 12 ዓመታት ሲሞከር እንደነበር የገለጹት ተመራማሪው ከ3 ዓመታት ወዲህ ግን ተጨባጭ ለውጥ በማምጣቱ እንዲስፋፋ እየተደረገ ነው ብለዋል። በጅማ ዞን የዴዶ ወረዳ ነዋሪው አርሶ አደር ቢያ ሀጂ፤ በምርምር ውጤቱ የተገኘውን ማዳበሪያ ተጠቅመው ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ በተሰጣቸው ሥልጠና መሠረትም ወደ ማምረት ሥራ ገብተው 10 ኩንታል የባዮቻር የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማምረታቸውን ገልጸዋል። ሌላው የወረዳው አርሶ አደር ራያ አባፊጣ ፤ተመራማሪዎቹ ባቀረቡት የተፈጥሮ ማዳበሪያን ተጠራጥረው እንደነበር ገልጸው፤ ሆኖም ውጤታማ መሆኑን ካወቅኩ በኋላ መጠቀም ብቻ ሳይሆን ወደ ማምረት ስራ ገብቻለሁ ብለዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያውን በአጭር ጊዜ ውስጥ በሁሉም የጅማ ዞን ወረዳዎች ለማዳረስ እንዲሁም በጥቂት ዓመታት ውስጥ ደግሞ ወደ ሌሎች አካባቢዎች ለማስፋፋት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑም ተገልጿል።
የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ለዲጂታል ኢትዮጵያ ግንባታ ያላቸውን ሚና ለማጠናከር ትኩረት ተሰጥቷል
Apr 14, 2026 518
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፦የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ለዲጂታል ኢትዮጵያ ግንባታ ያላቸውን ሚና ለማጠናከር ትኩረት መሰጠቱን በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የትምህርትና ክህሎት ለሥራ (ኢዝ) ፕሮጀክት አስተባባሪ ገለጹ። በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የትምህርትና ክህሎት ለሥራ (ኢዝ) ፕሮጀክት ለ12 ክልሎች እና ሁለት ከተማ አስተዳደሮች የሥራና ክህሎት ቢሮዎች የአይ ሲ ቲ መሰረተ ልማት ድጋፎች አድርጓል። ሚኒስቴሩ ድጋፍ ካደረጋቸው መካከል ኮምፒውተሮች፣ የኔትወርክ መሰረተ ልማት ቁሳቁሶች፣ ለቪዲዮ ኮንፍረንስ የሚያገለግሉ ቴሌቪዥኖች፣ የኤሌክትሪክ ማመንጫ ጄኔሬተሮችና የሶላር ፓኔሎች ይገኙበታል። በሚኒስቴሩ የኢዝ ፕሮጀክት አስተባባሪና የኢፌዴሪ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር ሀፍቶም ገብረእግዚአብሄር እንዳሉት፤ የሥልጠና ማዕከላትን በዘመናዊ መንገድ በኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ የመሰረተ ልማት ማሟላት ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል። ለአብነትም ሚኒስቴሩ ከልማት አጋሮች ጋር በመተባበር 70 ኮሌጆች አስፈላጊው መሰረተ ልማት እንዲሟላላቸው መደረጉን ጠቁመው፤ በዚህም የሥልጠና አቅምን ከፍ ያደረጉ ውጤቶች እየተገኘበት ነው ብለዋል። ዛሬ ፕሮጀክቱ ለ12ቱ ክልሎችና ለሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች ድጋፍ ያደረገው የአይ ሲ ቲ መሰረተ ልማቶች ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሂደት ዓይነተኛ ሚና እንዳለውም አክለዋል። ድጋፉ እንደ ሀገር ተግባራዊ በመደረግ ላይ ያለው የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና መርሃ ግብርን ስኬታማ ከማድረግ አኳያ ፋይዳ እንዳለውም አብራርተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ ዳግማዊት ግርማ፤ ወጣቱ የዲጂታል ክህሎት አዳብሮ የርቀት ሥራዎች (ሪሞት ጆብስን) ጨምሮ አዳዲስ የሥራ ዕድሎች ተጠቃሚ እንዲሆን እየሰራን ነው ብለዋል። የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማቶች መገኘታቸው ለሥራው መቃናት ትልቅ አበርክቶ እንዳለው ተናግረዋል። የኦሮሚያ ክልል ሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ነስረዲን ቃዲ በበኩላቸው፤ በክልሉ ከመደበኛ ስልጠና ባሻገር የነዋሪዎችን የዲጂታል ክህሎት ለማሳደግ ያለመ ሕዝባዊ ስልጠና መርሃ ግብር ተጀምሯል ብለዋል። ዛሬ የተገኘው ድጋፍ ሥራውን ውጤታማ በሆነ መልኩ ለመፈጸም ትልቅ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዓለሙ ገብሬ እንደገለጹት፤ ድጋፉ በክልሉ የሚገኙ የሥልጠና ማዕከላት ሥልጠናዎችን በጥራትና ዘመናዊ በሆነ መልኩ ተደራሽ እንዲያደርጉ ተጨማሪ አቅም ይፈጥራል።
ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች ለመላው አፍሪካ ኩራት ናቸው
Apr 14, 2026 286
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ) ፦ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች ለመላው አፍሪካ ኩራት ናቸው ሲሉ የላይቤሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳራ ቤይሶሎው ኒያቲ ገለፁ። ኢትዮጵያ በውጭ አገልግሎት አሰጣጥ (outsourcing) እና በፈጠራ ዘርፍ በአህጉሪቱ ተወዳዳሪና የማይበገር አቅም እየገነባች መሆኑንም ገልጸዋል። የላይቤሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሳራ ቤይሶሎው ኒያ የተመራ ልዑክ የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፓርክን ጎብኝቷል። ሚኒስትሯ ሳራ ቤይሶሎው ኒያ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ዘርፍ የታዩ ለውጦች ለመላው አፍሪካ ኩራት ናቸው። ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ ያላቸውን የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ያላቸውን ፍላጎትም ገልጸዋል። በተለይም በቴክኖሎጂ፣ በግብርና እና በትምህርት ዘርፎች ላይ በትብብር በመሥራት የሁለቱን አገራት ሕዝቦች ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚገባም አስረድተዋል። አፍሪካ ያላትን ሰፊ የሰው ሀይል በተለይም የወጣቶችን ኃይል በአግባቡ ለጠቀም በ"ደቡብ-ደቡብ" አገራት መካከል ያለው ትብብር ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመዋል። በአፍሪካ ደረጃ በጋራና በቅንጅት ከተሰራ አህጉሪቷን በልማት ማሳደግ እንደሚቻል አጽንኦት ሰጥተዋል። በአይ ሲቲ ፓርክ የተመለከቷቸውን የዳታ ማዕከላት አስመልክተው ኢትዮጵያ በውጭ አገልግሎት አሰጣጥ (outsourcing) እና በፈጠራ ረገድ በአህጉሪቱ ተወዳዳሪና የማይበገር አቅም እየገነባች መምጣቷን ገልፀዋል። በተለይም ወጣቶች አዳዲስ ግኝቶችን እንዲያመነጩ በፓርኩ ውስጥ የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ለሌሎች አገራት ምሳሌ የሚሆን ነው ብለዋል። በተለይም የዳታ ማዕከሉ አፍሪካ የራሷን መረጃ በራሷ አቅም የመያዝ ብቃት እንዳላት ማሳያ መሆኑንም ገልጸው፤ ላይቤሪያ ከኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ተሞክሮ በመቀመር የራሷን የዳታ ማከማቻ ማዕከል ለመገንባት ያላትን ፍላጎት አረጋግጠዋል። ጉብኝቱ በሁለቱ ጥንታዊ አፍሪካዊ አገራት መካከል ያለውን ታሪካዊ ግንኙነት ወደ ተግባራዊ የኢኮኖሚ እና የቴክኖሎጂ አጋርነት የሚያሸጋግር መሆኑ ተመላክቷል። በላይቤሪያው ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ የተመራ ልዑክ ለስራ ጉብኝት ትናንት ማምሻውን አዲስ አበባ መግባቱ ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የላይቤሪያው ፕሬዝዳንት ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ አቀባበል አድርገውላቸዋል።
የኮደርስ ስልጠና ቀልጣፋና ዘመናዊ የሕዝብ አገልግሎት መስጠት አስችሏል
Apr 14, 2026 223
ጅማ፤ ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡- በጅማ የኮደርስ ስልጠና የወሰዱ የመንግሥት ሠራተኞች ቀልጣፋና ዘመናዊ የሕዝብ አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ እያገዛቸው መሆኑን ገለጹ። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ የሆነው የ 5 ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በጅማ ከተማ በሚገኙ የተለያዩ የመንግሥት ተቋማት ሠራተኞች ዘንድ ትልቅ መነቃቃትን እየፈጠረ መሆኑ ተመልክቷል። ስልጠናው የሠራተኞችን የዲጂታል ክህሎት በማሳደግ፣ ቀልጣፋና ዘመናዊ የሕዝብ አገልግሎት ለመስጠት ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑም ተገልጿል። ሰራተኞቹ እንደሚናገሩት፤ የስልጠናው መርሃ ግብር በሥራቸው ላይ ተጨማሪ ዕውቀትና ክህሎት ጨምሮላቸዋል። በኢፌዲሪ የግል ድርጅቶች ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር የጅማ ዲስትሪክት ሠራተኞች የሆኑት ምህረት ካሳ እና ቁምነገር ወርቅዬ፣ ተቋሙ የኮምፒውተርና የኢንተርኔት አገልግሎትን ምቹ በማድረጉ የተለያዩ ኮርሶች መውሰዳቸውን ይናገራሉ። ከስልጠናው በኋላም በተቋሙ ውስጥ ለሚሰሩት ሥራ ትልቅ እገዛ ማድረጉን ገልጸዋል። በተጨማሪም ዓለም አቀፍ የሥልጠና ሰርተፊኬት ማግኘት መቻላቸውን ጠቅሰው፣ ሌሎች ሠራተኞችም ዕድሉን እንዲጠቀሙበት መክረዋል። የዲስትሪክቱ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መስፍን መሸሻ በበኩላቸው፣ ከተቋሙ 140 ሠራተኞች መካከል 70 በመቶ የሚሆኑት ስልጠናውን መውሰዳቸውን ገልጸዋል። ቀሪዎቹም ስልጠናውን እንዲያገኙ የግንዛቤ ማስጨበጥና የቴክኖሎጂ አቅርቦትን የማመቻቸት ሥራ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በጅማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ውስጥ የሚሰሩት ሙስሊማ አወል እና መሐመድ ኃይደር፣ አገልግሎቶች ወደ ዲጂታል እየተቀየሩ ባለበት በዚህ ወቅት ስልጠናው እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። "ከመደበኛ ሥራችን ጎን ለጎን ስልጠናውን መውሰዳችን ሥራችንን ይበልጥ ለማቀላጠፍና ለማስፋት እያገዘን ነው" ብለዋል። የማዕከሉ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አብዲ ሰለሞን እንደገለጹት፣ ከተቋሙ 104 ሠራተኞች መካከል 80 ያህሉ ስልጠናውን አጠናቅቀው ሰርተፊኬት ወስደዋል። ስልጠናው ሠራተኞች ለማኅበረሰቡ የሚሰጡት አገልግሎት በእውቀት ላይ የተመሠረተና ፈጣን እንዲሆን እያስቻለ መሆኑንም አክለዋል።
መደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎችን የፈጠራ ክህሎት ማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነ ነው
Apr 13, 2026 238
ሮቤ፣ ሚያዝያ 5/2018 (ኢዜአ)፦ የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂና የፈጠራ ዝንባሌ ያላቸው ተማሪዎችን ለተሻለ ውጤት ማብቃት የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን አስታወቀ። ዩኒቨርሲቲው ከስቴም (STEM) ማዕከል ጋር በመተባበር ባዘጋጀው አውደ ርዕይ ላይ፣ በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ኢንጂነሪንግ እና ሒሳብ ዘርፎች ሥልጠና የወሰዱ የሮቤ ከተማ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች የፈጠራ ሥራዎቻቸውንና ግኝቶቻቸውን በማቅረብ ላይ ይገኛሉ። በመርሐግብሩ ላይ የተገኙት የዩኒቨርሲቲው ምክትል ፕሬዚዳንት ረዳት ፕሮፌሰር ኢሳ ሐሰን እንደገለጹት፤ ተቋሙ የአካባቢውን ማኅበረሰብ ፍላጎትና ችግር መሠረት ያደረጉ ምርምሮችንና አገልግሎቶችን እያከናወነ ይገኛል። ዩኒቨርሲቲው ከ"ስቴም ፓዎር" (STEMpower) ድርጅት ጋር በመተባበር ያቋቋመው ቤተ-ሙከራ፣ በዘርፉ የሚታዩ ተግዳሮቶችን በመፍታት ረገድ ትልቅ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ገልጸዋል። ቤተ-ሙከራው ተማሪዎች በንድፈ-ሀሳብ የተማሩትን በተግባር እንዲለማመዱ በማድረግ፣ ሀገራዊና አካባቢያዊ ችግሮችን የሚፈታ ትውልድ ለመቅረጽ እያገዘ መሆኑን ጠቅሰዋል። የሮቤ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ጀማል አባገሮ በበኩላቸው፣ አውደ ርዕዩ ተተኪው ትውልድ የፈጠራ አቅሙን እንዲያጎለብት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል። የስቴም ፓዎር ኢትዮጵያ የኦፕሬሽን ማኔጀር አቶ አንተነህ ፍሰሃ በ"ዲጂታል ኢትዮጵያ" ስትራቴጂ አማካኝነት በሀገር ደረጃ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ አበረታች ለውጦች እየታዩ መሆኑን ገልጸዋል። ይህ አውደ ርዕይ የተማሪዎችን ዝንባሌ ከማሳደግ ባለፈ፣ ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስኬት ጉልህ ድርሻ እንደሚኖረውም አክለዋል። በአውደ ርዕዩ ላይ የተሳተፉ ተማሪዎች በአካባቢያቸው የሚገኙ ቁሳቁሶችን በመጠቀም፣ ለችግር ፈቺ የሆኑ የቴክኖሎጂ ዲዛይኖችን አቅርበዋል። ተማሪዎቹ እንዲህ ያሉ መድረኮች ክህሎታቸውን ለማሳደግና ለወደፊት የፈጠራ ሥራዎቻቸው መነሳሳትን እንደሚፈጥሩላቸው ገልጸዋል። የሳይንስና ቴክኖሎጂ አውደ ርዕይ ነገም ቀጥሎ እንደሚውል ታውቋል።
ኢትዮጵያ በዲጂታል ዘርፍ ያሳየችው ፈጣን ሽግግር እና ያስመዘገበችው ውጤት ለአህጉሪቱ ምሳሌ ነው
Apr 10, 2026 447
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በዲጂታል ዘርፍ ያሳየችው ፈጣን ሽግግርና ያስመዘገበችው ውጤት ለአህጉሪቱ ምሳሌ መሆኑን በአፍሪካ ስታትስቲክስ ኢንስቲትዩት የኢኮኖሚ ስታትስቲክስ ዳይሬክቶሬት ኃላፊ አዱም ጋጎሉም ገለጹ። ኃላፊው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፣ ከአህጉሪቱ ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት 65 በመቶውን አስተዋጽኦ የሚያደርገውን መደበኛ ያልሆነ የኢኮኖሚ ዘርፍ ለመደገፍ ዲጂታላይዜሽን ወሳኝ ነው። በኢትዮጵያ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎችን የፋይናንስ ተጠቃሚ ያደረጉት እንደ ቴሌ ብር እና ሲቢኢ ብር ያሉ የቴክኖሎጂ ውጤቶች በአጭር ጊዜ ውስጥ ያመጡት ለውጥ እጅግ አስደናቂና አበረታች መሆኑን በምሳሌነት ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲ ለመክፈት የጀመረችው ስራ ለአህጉሪቱ አዲስ ተስፋ የሚሰጥ መሆኑንም አንስተዋል። ኢትዮጵያ ተግባራዊ ያደረገችው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም እና የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ፖሊሲዎች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑንም ተናግረዋል። በተለይም ዓለም አቀፋዊ ተወዳዳሪነትን ለማስፈን እንደ ቴሌኮም እና ባንክ ያሉ ቁልፍ ዘርፎች ለውጭ ኢንቨስትመንት ክፍት መደረጋቸው የሀገሪቱን የሊብራላይዜሽን ጉዞ የሚያፋጥን ትክክለኛ ውሳኔ ነው ብለዋል። የተመዘገቡት የልማት ስኬቶችና የመሰረተ ልማት ግንባታዎች፣ በፈረንጆቹ 2063 የበለጸገች አፍሪካን እውን ለማድረግ ትልቅ ሚና እንደሚኖራቸው አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ እያሳየች ያለው ፈጣን ለውጥ በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ከቀጠለ፣ አፍሪካ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተሰሚነትና ክብር ከፍ እንደሚያደርገው አብራርተዋል። የዓለም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት (IMF) የስታትስቲክስ ዲፓርትመንት ምክትል ዳይሬክተር ጂም ቴብራክ፣ ዲጂታላይዜሽን የፋይናንስ ተደራሽነትን በማስፋት ለዓለም ኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል።። በኢትዮጵያ በዲጂታላይዜሽን መስፋፋት እየታየ ያለው እንቅስቃሴ በጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በአሁኑ ወቅት ዓለም በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘመን ላይ በመሆኗ፣ ሀገራት በጤና፣ በትምህርትና በንግድ ዘርፎች ተጠቃሚ ለመሆን አስፈላጊውን ዝግጅት ማድረግ እንዳለባቸውም አጽንኦት ሰጥተዋል። ይህ የዲጂታል ለውጥ የፋይናንስ አገልግሎት ባልደረሰባቸው አካባቢዎች ጭምር ቀላልና ፈጣን አማራጮችን በማስፋፋት፣ ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማምጣት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት ነው ያብራሩት።
የክፍያ ስርዓቱ የትራንስፖርት ዘርፍ አገልግሎቱን በማዘመን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴን ለማሳለጥ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር ነው
Apr 9, 2026 148
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮ-ቴሌኮም ያስጀመረው የክፍያ ስርዓት የትራንስፖርት ዘርፍ አገልግሎትን በማዘመን የሀገርን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለማሳለጥ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር መሆኑ ተገለጸ። ኢትዮ-ቴሌኮም "ቶሎ" የተሰኘ ዲጂታል የክፍያ ስርዓት ዛሬ አስጀምሯል። የዲጂታል ክፍያ ስርዓቱ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ እና የኢትዮጵያ ክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሙስጠፋ አባሲመል በቱሉ ዲምቱ ዋና የክፍያ ጣቢያ አስጀምረዋል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ ተቋሙ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የሚያስችሉ የተለያዩ አገልግሎቶችን ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል። ኢትዮ-ቴሌኮም ከመደበኛ የቴሌኮም አገልግሎት ባሻገር ቀልጣፋ፣ ምቹና ወጪ ቆጣቢ አገልግሎት በማቅረብ የፋይናንስ ዘርፉን እየደገፈ መሆኑንም አስረድተዋል። በዚህም የሀገርን ልማት ዘላቂና አካታች ለማድረግ የዲጂታል መሰረተ ልማት ዝርጋታ ላይ ትኩረት በማድረግ በርካታ ተግባራት ማከናወኑን ገልጸዋል። ኢንተርፕራይዙ በቀን ከ32 ሺህ በላይ ተሽከርካሪዎችን የሚያስተናግድ እንደመሆኑ፣ አዲሱ የ"ቶሎ" ዲጂታል ክፍያ አሠራር ጊዜን ከመቆጠብ ባሻገር የአገልግሎት ጥራትንና የመንገድ ደኅንነት ቁጥጥርን ማረጋገጥ የሚያስችል ነው። በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ሥር የሚገኘው ይህ ተቋም፣ አገልግሎቱን 100 በመቶ ዲጂታል ለማድረግና አረንጓዴ ኢነርጂን ተግባራዊ ለማድረግ እየሠራ እንደሚገኝም ተመላክቷል። ዛሬ የተጀመረው የዲጂታል ክፍያ መርሃ ግብርም የትራንስፖርት ዘርፉን አገልግሎት በማሳለጥ የሀገርን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለማሳደግ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር ነው ብለዋል። ይህም ደንበኞች ለዚሁ ዓላማ የተዘጋጀ ካርድ ተጠቅመው ክፍያ እንዲፈጽሙ የሚያስችል መሆኑ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሙስጠፋ አባሲመል በበኩላቸው፤ ካሁን ቀደም ወረቀት መሰረት ያደረገ ክፍያ ስርዓት ይከናወን እንደነበረ ገልፀዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ ማስደገፍ አስፈላጊ መሆኑን አመልክተው፤ አገልግሎቱ ሙሉ ለሙሉ ዲጂታላይዝ የማድረግ ጉዞ ዛሬ መጀመሩን ይፋ አድርገዋል። "ቶሎ" የተሰኘ የክፍያ ስርዓት ሶፍትዌር መልማቱን አመልክተው፤ ይህም ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በመተባበር ከቴሌ ብር ጋር በማስተሳሰር ዘመናዊ የክፍያ ስርዓት መጀመሩ አብስረዋል። በዚህም ደንበኞች የተዘጋጀውን ካርድ በመጠቀም ክፍያ እንዲፈፅሙ በማስቻል ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንደሚያገኙ ተናግረዋል። የክፍያ ስርዓቱ የመንግሥት አገልግሎቶችን በማዘመን ግልጽና የአሰራር ቅልጥፍና የሰፈነበት የዲጂታል ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለውን ቁርጠኝነት በተግባር የሚያሳይ ነው ብለዋል። ሁለቱ ተቋማት በቀጣይ አብሮ መስራት የሚያስችል የስምምነት ፊርማ ስነ-ስርዓት አካሂደዋል።
ዲጂታል ኢንሼቲቩ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት መፋጠን ያለው ፋይዳን በመገንዘብ በባለቤትነት መንፈስ ሊተገበር ይገባል -ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Apr 9, 2026 221
ባህርዳር፤ ሚያዚያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ የክልሉ አመራር ዲጂታል ኢንሼቲቩ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት መፋጠን ያለው ፋይዳ በመገንዘብ በባለቤትነት መንፈስ ሊተገብረው እንደሚገባ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ አሳሰቡ። ርዕሰ መስተዳድሩ በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያና ኢትዮ ኮደርስ አፈጻጸም ያለበትን ሁኔታ በመገምገም ቀጣይ የስራ መመሪያ አስተላልፈዋል። ርዕሰ መስተዳድር አረጋ በመድረኩ ላይ ባስተላለፉት መልእክት የመንግስት ተቋማትን አሰራር ፈጣንና ቀልጣፋ ለማድረግ የዲጂታል አሰራርን መተግበር ይገባል ብለዋል። በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያና ኢትዮ ኮደርስ ኢንሼቲቮች የዲጂታል ትራንስፎርሜሽኑን የሚያረጋግጡ መሆናቸውን ገልጸዋል። አመራሩም ኢንሼቲቮቹ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት መፋጠን ያላቸውን ፋይዳ በመገንዘብ በባለቤትነት መንፈስ ሊተገብራቸው እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የትምህርትና ጤና ሴክተር ሰራተኞችን ጨምሮ ሁሉም የመንግስት ሰራተኞች በዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ላይ በንቃት መሳተፍ እንዳለባቸው አመልክተዋል። የዲጂታል ትግበራው አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል፣ የዜጎችን ደህንነት ለማረጋገጥ፣ አለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ለማጎልበት በተሟላ ሁኔታ መተግበር አለበት ብለዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአማራ ክልል የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር) በበኩላቸው እየተተገበሩ የሚገኙት ኢንሸቲቮች የክልሉን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ የሚያፋጥኑ ሞተሮች መሆናቸውን ተናግረዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በርካታ ተቋማት በአንድ ማእከል አገልግሎታቸውን ለህብረተሰቡ በማቅረብ ይነሳ የነበረውን የመልካም አስተዳደር ችግር ለመቅረፍ ማስቻሉን አክለዋል። ፋይዳ የዲጂታል መታወቂያን እስካሁን 5 ነጥብ 3 ሚሊዮን የክልሉ ነዋሪዎች መውሰዳቸውን ጠቁመው፤ በቀጣይ ሦስት ወራትም ቀሪ ግቦችን ለማሳካት የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። የክልሉ ሲቪል ሰርቪስና ሰው ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ ወይዘሮ ባንችአምላክ ገብረማሪያም፤ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የኢትዮ ኮደርስና የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት እንደሚያስችሉ አስረድተዋል። በመድረኩ ላይ ዘርፎቹን የሚመሩ አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
ኢትዮ ቴሌኮም "ቶሎ" የተሰኘ የፈጣን መንገድ የክፍያ ሥርዓትን በቴሌ ብር ማከናወን የሚያስችል ዲጂታል የክፍያ ስርዓት አስጀመረ
Apr 9, 2026 306
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮ ቴሌኮም "ቶሎ" የተሰኘ የፈጣን መንገድ የክፍያ ሥርዓትን በቴሌ ብር አገልግሎት መስጠት የሚያስችለውን ዲጂታል የክፍያ ስርዓት አስጀመረ። ኢትዮ ቴሌኮም "ቶሎ" የተሰኘ የፈጣን መንገድ የክፍያ ሥርዓትን በቴሌ ብር ማከናወን የሚያስችለውን ዲጂታል የክፍያ ስርዓት የማስጀመር መርሀ ግብር በቱሉ ዲምቱ ዋና የክፍያ ጣቢያ እያካሄደ ነው። የክፍያ ስርዓቱን የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ እና የኢትዮጵያ ክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሙስጠፋ አባሲመል በቱሉ ዲምቱ ዋና የክፍያ ጣቢያ አስጀምረዋል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ ተቋሙ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የሚያስችሉ የተለያዩ አገልግሎቶችን ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል። ኢትዮ-ቴሌኮም ከመደበኛ የቴሌኮም አገልግሎት ባሻገር ቀልጣፋ፣ ምቹና ወጪ ቆጣቢ አገልግሎት በማቅረብ የፋይናንስ ዘርፉን እየደገፈ መሆኑንም አስረድተዋል። በዚህም የሀገርን ልማት ዘላቂና አካታች ለማድረግ የዲጂታል መሰረተ ልማት ዝርጋታ ላይ ትኩረት በማድረግ በርካታ ተግባራት ማከናወኑን ገልጸዋል። ዛሬ የተጀመረው አገልግሎት የትራንስፖርት ዘርፉ በተሻለ ደረጃ አገልግሎት እንዲሰጥ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር ነው ብለዋል። ይህም ደንበኞች ለዚሁ ዓላማ የተዘጋጀ ካርድ ተጠቅመው ክፍያ እንዲፈጽሙ የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። የኢትዮጵያ የክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈፃሚ ሙስጠፋ አባሲመል በበኩላቸው፤ ካሁን ቀደም ወረቀትን መሰረት ያደረገ ክፍያ ስርዓት ይከናወን እንደነበር ገልፀዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ ማስደገፍ አስፈላጊ መሆኑን አመልክተው፤ አገልግሎቱን ዲጂታላይዝ የማድረግ ጉዞ ዛሬ መጀመሩን ይፋ አድርገዋል። "ቶሎ" የተሰኘ የክፍያ ስርዓት ሶፍትዌር መልማቱን አመልክተው፤ በዚህም ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በመተባበር ከቴሌ ብር ጋር በማስተሳሰር ዘመናዊ የክፍያ ስርዓት መጀመሩን አብስረዋል። በዚህም ደንበኞች የተዘጋጀ ካርድ በመጠቀም ክፍያ እንዲፈፅሙ በማስቻል ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንደሚያገኙ ተናግረዋል። ሁለቱ ተቋማት በቀጣይ አብሮ መስራት የሚያስችል የፊርማ ስምምነት ስነ-ስርአትም አካሂደዋል።
በክልሉ ለዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት የመስጠት ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Apr 9, 2026 129
ባህርዳር ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የዲጂታል አገልግሎቶችን በማስፋት ለዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት የመስጠትና ብልሹ አሰራሮችን የመከላከል ጥረት ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አሕመዲን መሀመድ (ዶ/ር) ገለጹ። በአማራ ክልል የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት፣ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያና የኢትዮ ኮደርስ አፈጻጸም ያለበትን ሁኔታ የሚገመግም መድረክ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ ላይ የተገኙት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አሕመዲን መሀመድ (ዶ/ር)፤ በክልሉ የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በተመረጡ ከተሞች ተጀምሮ ለሌሎች አካባቢዎችም ሞዴል በሚሆን መልኩ እየተሰራበት ይገኛል ብለዋል። የፋይዳ የዲጂታል መታወቂያና የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን ተደራሽ በማድረግ ረገድም ጥሩ አፈፃፀም መመዝገቡን ገልጸዋል። በክልሉ እስካሁን 5 ነጥብ 3 ሚሊዮን ዜጎች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ መውሰዳቸውንም ለአብነት ጠቅሰዋል። እነዚህ አገልግሎቶች ተግባራዊ መደረጋቸው ለዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እንዲሁም ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከል አስችሏል ብለዋል። በቀጣይም አገልግሎቶቹን ተደራሽነት የማስፋት ስራ ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በመድረኩ ላይ በክልሉ የሚገኙ ዘርፉን የሚመሩ የተለያዩ የቢሮ ኃላፊዎችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የዲጅታል ልማት ስትራቴጂ ትልቅ ስኬት የተመዘገበበት ነው
Apr 8, 2026 154
መቀሌ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የዲጅታል ልማት ስትራቴጂ ትልቅ ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ተናገሩ። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ትግበራ በስኬት መጠናቀቁን ተከትሎ በቀጣይ አምስት ዓመታት የሚከናወን ቀጣይነት ያለው ስትራቴጂክ ፕላን ይፋ በማድረግ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩ ይታወቃል። የ2025 ስትራቴጂክ ተግበራ ስኬት ተደርገው ከሚወሰዱት መካከል የባንኮች የዲጅታል አገልግሎት መሳለጥ፣ የቴሌብር አገልግሎት፣ የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ፣ የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ስልጠና እና ሌሎችም ይገኙበታል። የአርቲፊሻል ኢንተሊጀንስ፤ የአዳዲስ ፈጠራዎች፣ የተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ በዲጅታል የታገዙ መሆናቸውም ለዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ማሳያዎች መሆናቸውን መግለጽ ይቻላል። ከዚህ ስኬትም በመነሳት የዲጅታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ይፋ ተደርጎ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በመደረግ ላይ ይገኛል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ በትግራይ ክልል ያነጋገራቸው የዘርፉ ባለሙያዎች በዲጅታል ልማት ባለፉት አምስትና ስድስት ዓመታት የተከናወኑ ተግባራት አስደናቂ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከባለሙያዎቹ መካከል ሰሎሞን ፀጋይ፤ በተለይም የቴሌብር አገልግሎት፣ የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ፣ የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ስልጠና ለዘርፉ መሰረት ያኖሩ መሆናቸውን አስረድተዋል። የተቋማት የዲጅታል አገልግሎት እየተስፋፋ መምጣት ሌላኛው ስኬት መሆኑንም ጠቅሰዋል። ከዚህ ስኬት በመነሳትም በቀጣይ አምስት አመታት የሚተገበረው ስትራቴጂክ እቅድ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርጋት መሆኑን ገልጸዋል። የድጅታል ቴክኖሎጂ ምርምርና ጥናት ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት አቶ ሰሎሞን ገብረመድህን በበኩላቸው በተለይም ወጣቶች የኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸው ለዘርፉ ልማትና አድገት ትልቅ አቅም መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የዲጅታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ እቅድን ለማሳከት ስልጠናዎች እንዳሉ ሆነው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና የዘርፉ ባለሙያዎች በጥናትና ምርምር የተደገፈ ስራ ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። ሌላኛው የቴክኖሎጂ ባለሙያ ሀጎስ ገብረፃድቅ፤ በዲጅታል ቴክኖሎጂ እንደ ሀገር የተከናወኑ ተግባራትና በቀጣይ የተያዙ እቅዶች የሚያጓጉ መሆኑን ገልጸዋል። በገጠርና በከተሞች የዲጅታል አገልገግሎትን በማስፋት ዜጎች ፈጣን፣ ፍትሃዊና ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ መትጋት ይጠበቅብናል ብለዋል። በአገልግሎት አሰጣጥ ሂደት ሌብነትና ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከልም የዲጅታል ትግበራ የማይተካ ሚና የሚኖረው መሆኑን አስረድተዋል።
የአርማወር ሐንሰን ምርምር ኢንስቲትዩት ችግር ፈቺ የምርምርና ፈጠራ ውጤቶችን እያበረከተ ነው
Apr 7, 2026 241
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 29/2018 (ኢዜአ)፦የአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት በሳይንሳዊ ምርምርና በፈጠራ ሥራዎች በሀገርና በአህጉር ደረጃ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡ ውጤቶችን እያስመዘገበ መሆኑን የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአርማወር ሐንሰን የምርምር ተቋም የተገነባውንና ዘመናዊ መሠረተ ልማቶችን የያዘውን የምርምር ማዕከል መጋቢት 26 ቀን 2018 ዓ.ም መርቀው ከፍተዋል። በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክትም ማዕከሉ ኢትዮጵያና አፍሪካ በሳይንሱ ዘርፍ ወደ አዲስ ምዕራፍ እንዲሸጋገሩ ትልቅ መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል። ይህ ዘመናዊ የምርምር ማዕከል ከመሠረተ ልማት ግንባታ ባለፈ፤ በመድሃኒትና በክትባት ራሷን የቻለችና ጤናማ የሆነች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የሚተጋ የላቀ የዕውቀት ሥፍራ መሆኑን ተናግረዋል። የአርማወር ሐንሰን ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ተቋሙ ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ በከፍተኛ አቅምና በውጤታማነት እየሠራ ነው። ኢንስቲትዩቱ ባለፉት ስምንት ዓመታት በተለይም እንደ ሳንባ ነቀርሳ (ቲቢ)፣ ወባ፣ ሚኒንጃይትስና ኒሞኒያ ባሉ ተላላፊ በሽታዎች ላይ ውጤታማ ጥናቶችን ማድረጉን ጠቅሰዋል። ለአብነትም የሳንባ ነቀርሳ ሕክምና ጊዜን ለማሳጠር የተደረገው ምርምር ለሕዝቡ የጤና ችግር ቀጥተኛ መፍትሔ የሚሰጥ ነው ብለዋል። ኢንስቲትዩቱ በዓለም አቀፍ የሳይንስ መድረክ ላይ የኢትዮጵያን አሻራ በጉልህ እያሳረፈ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በየዓመቱ ከ80 እስከ 100 የሚደርሱ የምርምር ሥራዎች በታዋቂ የሳይንስ መጽሔቶች ላይ እንዲታተሙ በማድረግ ኢትዮጵያንና አፍሪካን በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ በስፋት እያስተዋወቀ ነውም ብለዋል። የተጠናቀቁና ውጤታማነታቸው የተረጋገጠ ምርምሮችም በቅርቡ ለሕዝብ ይፋ እንደሚሆኑ ፕሮፌሰር አፈወርቅ አረጋግጠዋል። ትኩረቱን ይበልጥ በማስፋት ከተላላፊ በሽታዎች በተጨማሪ በአሁኑ ወቅት በስፋት እየታዩ ባሉ ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ላይ ጥናቶችን እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ኢንስቲትዩቱ ከጤና ዘርፍ ባለፈ ከሀገር ውስጥ አምራች ኢንዱስትሪዎችና ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር በመተባበር የተለያዩ የሕክምና መሣሪያዎችን በማምረት ላይ እንደሚገኝም አንስተዋል።
ዩኒቨርሲቲው የአፈር ለምነትን መጠበቅ የሚያስችሉ የምርምር ስራዎችን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥቷል
Apr 4, 2026 341
ወላይታ ሶዶ፤ መጋቢት 26/2018(ኢዜአ)፦ ወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የአፈር ለምነትን መጠበቅ የሚያስችሉ የምርምር ስራዎችን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ መሆኑን አስታወቀ። በዩኒቨርሲቲው "የአፈር ለምነትንና ጤናማነትን ማስጠበቅ ለግብርና ሽግግር" በሚል መሪ ሃሳብ 14ኛው ዙር ዓመታዊ ሀገር አቀፍ የምርምር ኮንፍረንስ ተካሂዷል። በወቅቱ በዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት አክበር ጩፎ(ዶ/ር) እንደገለፁት፤ ዩኒቨርሲቲው የአፈር ለምነትን መጠበቅ የሚያስችሉ የምርምር ስራዎችን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ ይገኛል። የአፈር ለምነትና ጤናማነትን መጠበቅ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት የሚያሳድግ በመሆኑ ለግብርና ዘርፍ ምርምሮች ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። በመሆኑም ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ስራው ጎን ለጎን በዘርፉ የተሰማሩ ተመራማሪዎችን በመደገፍ የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በበጀት ዓመቱ ከ79 ሚሊየን ብር በላይ በጀት በመመደብ ከ50 በላይ የምርምር፣ 54 የማህበረሰብ ተኮር እንዲሁም ከ14 በላይ የቴክኖሎጂ ሽግግር ስራዎችን እየሰራ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የዩኒቨርሲቲው ምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት ዘውድነህ ቶማስ(ዶ/ር) ናቸው። በዩኒቨርሲቲው ያለውን ዕውቀት ከሀብት ጋር ለማቀናጀት ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ ስለመሆኑም ገልጸዋል። በዚህም የዘንድሮው 14ኛው ዓመታዊ የምርምር ኮንፍረንስ የአፈር ጤንነትና ምርታማነት ላይ አተኩሮ መዘጋጀቱን ጠቁመው በዘርፉ የተሰማሩ ምሁራንና ባለሙያዎች ቅንጅታቸውን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ኑሮ ለማሻሻል አበክረው መስራት እንዳለባቸውም አመልክተዋል። በዩኒቨርሲቲው የአፈር ሳይንስ ጥናት ፕሮፌሰር ፋኑኤል ላዕከማርያም ፅሁፍ ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት በአፈር ዙሪያ የሚደረጉ ምርምሮች ምርትና ምርታማነትን ከማሳደግ ባሻገር የሰው፣ የአካባቢ እና የእንስሳትን ጤና ለማስጠበቅ ቁልፍ ሚና ይጫወታሉ። በጥናታዊ ጽሁፋቸው የአፈር እርጥበትን ማስጠበቅ፣ አሲዳማነትን መቀነስ፣ ምርታማነትን መጨመርና ካርቦንን አምቆ የመያዝ አቅምን ማሳደግ ላይ ያተኮረ መሆኑን አመልክተዋል። በዚህም የተለያዩ ጥናቶች መስራታቸውን ጠቁመው ይህም መንግስት ዘርፉን ለማሻሻል የጀመረውን ውጥን የሚደግፍ በመሆኑ ወደ አርሶ አደሮች በማምጣት እንደሚተገበርም አስረድተዋል። በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የተፈጥሮ ሀብት አያያዝና የአየር ንብረጥ ለውጥ መቋቋም ፕሮግራም ዳይሬክተር አወቀ ሙሉዓለም(ዶ/ር) በበኩላቸው ተቋማቸው የሀገሪቱን ግብርና ለማሻገር በጥናት የተደገፈ ስራ በመስራት የግብርናን ትራንስፎርሜሽን ለማረጋገጥ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የተሻለ ውጤት በማስመዝገብ መንግስት በዘርፉ የያዘውን ውጥን ለማሳካት እየተጋ መሆኑን በመጥቀስ ለስራው ውጤታማነት ከመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በትብብር እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ይህም አርሶ አደሩ ከቤተሰብ ፍጆታ ያለፈ ትርፍ ምርት በማምረት ተጠቃሚ እንዲሆን እንዲሁም ገበያን በማረጋጋት በኩል አበርክቶ እንዲኖረው ትልቅ ድርሻ መወጣቱን አመልክተዋል። በመድረኩ ከ10 በላይ ጥናታዊ ጽሁፎች የቀረቡ ሲሆን ሙያዊ ውይይት ተደርጎ የፖሊሲ አቅጣጫ የማመላከት ስራ እንደሚሰራም ተገልጿል።
በምርምር ስራዎች የአደጋ ተጋላጭነትን ለመቀነስ የሚደረገው ጥረት ይጠናከራል
Apr 4, 2026 590
ሰመራ፣መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ) ፡-በምርምር ስራዎች የአደጋ ተጋላጭነትን ለመቀነስ የሚደረገውን ጥረት ማጠናከር እንደሚገባ የሠመራ ዩኒቨርሲቲ የምርምር ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ዓሊ ተናገሩ። በሰመራ ዩኒቨርሲቲ ለዘጠነኛ ጊዜ የተዘጋጀ የአደጋ ተጋላጭ ማህበረሰብ ዝግጁነትና መቋቋም ላይ ያተኮረ ሲምፖዚየም በሰመራ ከተማ ተካሄዷል። በመድረኩ ላይ ምክትል ፕሬዚዳንቱ እንደተናገሩት፤ የምርምር ስራዎችን በማጠናከርና ተግባራዊ በማድረግ የአደጋ ተጋላጭነትን ለመቀነስ የሚደረገውን ጥረት መደገፍ ይገባል። የምርምር ውጤቶቹ ማህበረሰቡን ከማንቃትና ተጋላጭ እንዳይሆኑ ከማድረግ አኳያ ሚናው ከፍተኛ መሆኑን አስረድተዋል። በተለይም ተመራማሪዎች፣ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ አካላት የአካባቢውን ችግር ተረድተው እገዛ ሊያደርጉ እንደሚገባ አመልክተው በአካባቢው የሚገነቡ ህንፃዎች ጭምር ግምት ውስጥ ሊገቡ እንደሚገባም አመልክተዋል። በሲምፖዚየሙ ላይ የተገኙት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመሬት መንቀጥቀጥ ተመራማሪና መምህር ፕሮፌሰር አታላይ አየለ በበኩላቸው፤ የተፈጥሮ አደጋዎች ከመከሰታቸው በፊት ዝግጅት ማድረጉ የጉዳት መጠኑን ለመቀነስ እገዛ ያደርጋል ብለዋል። የውይይት መድረኮችን በማዘጋጀት ውሳኔ ሰጪ አካላት ለጉዳዩ ትኩረት እንዲሰጡ ማድረግ፣ ፖሊሲዎችን ማጤንና የህንፃ ግንባታ ደረጃ ግልፅ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። መገናኛ ብዙሃን ጉዳዩን አስመልክተው እያከናወኑ ያለው የግንዛቤ ማስጨበጥ ተግባር ሊጠናከር እንደሚገባ ጠቁመው የምርምር ግኝቶችን በየጊዜው በማውጣት ለሚመለከታቸው አካላት ማጋራት ይገባል ብለዋል። በመድረኩም ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የመጡ ተመራማሪዎች፣ የትምህርት ሚኒስቴርና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያ በያዝነው ዓመት መድኃኒት የማምረት አቅሟን ከ50 በመቶ በላይ ታደርሳለች - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 4, 2026 208
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የሀገር ውስጥ መድኃኒት የማምረት አቅሟን፣ በ2018 ዓ.ም ከ50 እስከ 55 በመቶ ለማድረስ ማቀዷን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኢትዮጵያ እና በአፍሪካ የሳይንስ ሥነ-ምሕዳር ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ዘመናዊ የምርምር ማዕከልን ዛሬ መርቀው ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በአንድ ሀገር ጉዞ ውስጥ የሚያጋጥሙ ችግሮችንና ፈተናዎችን ወደ መልካም ዕድል መቀየር እጅጉን አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት፣ አፍሪካ ለከፍተኛ አደጋ ትጋለጣለች የሚል ግምት በበለጸጉት ሀገራት በኩል የነበረ ቢሆንም፣ ያ ሳይሆን መቅረቱን አመልክተዋል። ይሁን እንጂ ወረርሽኙ በሽታን አስቀድሞ የመከላከል ዝግጁነት ምን ያህል እንደሚያስፈልግ ትልቅ ትምህርት ሰጥቶ ማለፉን ተናግረዋል። በወቅቱ መንግስት በምግብ፣ በልብስ እና በመድኃኒት ዘርፎች ራስን መቻል አለብን የሚል ግልጽ አቅጣጫ ይዞ ወደ ሥራ መግባቱን አስታውሰዋል። በዚህም በምግቡ ዘርፍ ስንዴን ጨምሮ ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፣ በመድኃኒት በኩል ግን በሚፈለገው ደረጃ ለውጥ አለመታየቱን ጠቁመዋል። በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅት ኢትዮጵያ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ማምረት የምትችለው መድኃኒት ስምንት በመቶ ብቻ እንደነበርም አስታውሰዋል። በቂ የመድኃኒት ምርት ማምረት አለመቻሉ፣ ሻጮች የግዢ መድኃኒት መያዛቸውና የግሉ ዘርፍ በምርት ሂደቱ ላይ ለመሳተፍ እምብዛም ፍላጎት አለማሳየቱ በመንግስት በኩል ትልቅ ቁጭት እንዲፈጠር አድርጓል ብለዋል። በምግብ፣ በልብስና በመድኃኒት ራሱን ያልቻለ ሀገር የተሟላ ሉዓላዊነት እንደሌለው ጠቅሰው፣ ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባት የተከናወኑ ተግባራት ውጤት ማስገኘታቸውን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ማምረት የምትችለው የመድኃኒት ድርሻ ቀደም ሲል ከነበረበት ስምንት በመቶ አሁን ላይ ወደ 44 በመቶ ከፍ ማለቱን ገልጸዋል። በቅርብ ጊዜያት የሚመረቁ ፋብሪካዎችን ታሳቢ በማድረግም በተያዘው ዓመት የማምረት አቅሙ ከ50 እስከ 55 በመቶ እንደሚደርስም አስታውቀዋል። በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያ ቢያንስ መድኃኒትና ክትባትን በራሷ አቅም እንድታመርት በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በአንጋፋው የአርማወር ሐንሰን የምርምር ተቋም የተመረቀው ዘመናዊ የምርምር ማዕከል ከፍተኛ ወጪ የወጣበት መሆኑን ጠቁመው፣ ለማዕከሉ ለመድኃኒትና ክትባት ምርት መሠረት የሚጥሉ ዕውቀቶችን መያዙንም አመልክተዋል። በኮቪድ ወቅት የናሙና ምርመራ ወደ ደቡብ አፍሪካ ይላክ እንደነበር ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ አዲሱ የምርምር ማዕከል እንዲህ ያሉ ምርመራዎችን እዚሁ የማከናወን አቅም እንዳለው ገልጸዋል። ማዕከሉ 40 ላቦራቶሪዎችን፣ የላቁ የጂኖሚክስና ባዮኢንፎርማቲክስ ክፍሎችን እንዲሁም የመድኃኒቶችን ጥራት የሚያረጋግጥ የባዮኢኩዊቫለንስ ማዕከልን ያካተተ ሲሆን፤ ለድንገተኛ የጤና አደጋዎች ምላሽ የመስጠት አቅምን በመገንባት ረገድም እንደ ዋልታ የሚያገለግል መሆኑን አመልክተዋል። ምርምርን ወደ ፖሊሲ፣ ፈጠራን ደግሞ ወደ ተግባራዊ መፍትሔ በመቀየር ረገድ ማዕከሉ በመድኃኒት ምርት ራስን ለመቻልና ዘላቂ የጤና ደህንነትን ለማረጋገጥ የሚረዳ ትልቅ እርምጃ መሆኑን ገልጸዋል። በጥረትና በትጋት ከሰራን ሀገርን ማሳደግና ማበልጸግ እንደሚቻል ይህ ማዕከል ትልቅ ማሳያ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ እየተደረገ ባለው ጥረት አበረታች ውጤት እየተገኘ ነው
Apr 4, 2026 171
ደሴ፤ መጋቢት 26/2018(ኢዜአ)፦ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ እየተደረገ ባለው ጥረት አበረታች ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር) አስታወቁ። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከወሎ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በሳይንስና ቴክኖሎጂ ፖሊሲ፣ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 እና በስታርታፕ ፖሊሲ አዋጅ ዙሪያ የምክክር መድረክ አካሂዷል። ሚኒስትሩ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፣ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሁለንተናዊ እድገትን ለማፋጠን በትኩረት እየተሠራ ይገኛል። ባለፉት ዓመታት ለዚህ አጋዥ የሆኑ ፖሊሲዎችን፣ ስትራቴጂዎችንና መመሪያዎችን በማዘጋጀት ወደ ሥራ መገባቱ "ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025" እቅድን በስኬት ለማጠናቀቅ ማስቻሉን አውስተዋል። በተለይም በሪፎርም ማሻሻያዎችና በተቋማት ግንባታ፣ በመሠረተ ልማትና በሰው ኃይል ልማት፣ በኢንተርኔት ተደራሽነትና በዲጂታል ክፍያ አመርቂ ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰዋል። የተገኘውን ተሞክሮ በማስፋት "ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ስትራቴጂን በሳይንስና ቴክኖሎጂ፣ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (AI)፣ በጤና፣ በግብርና እና በሌሎች ቁልፍ ዘርፎች ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ሥራ ፈጣሪ ወጣቶችን በማበረታታትና ወደ ተግባር እንዲገቡ በማድረግ፣ ኢትዮጵያ በዲጂታል ዘርፍ መሪ እንድትሆን ጥረት እየተደረገ መሆኑንም አስረድተዋል። ለዚህ ውጤታማነትም ሚኒስቴሩ ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በቅንጅት እየሠራ መሆኑን ጠቁመው፣ የዛሬው መድረክም የተጀመሩ ተግባራትን ማጠናከር የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። የወሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አወል ሰይድ(ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ዩኒቨርሲቲው የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል። የዩኒቨርሲቲውን የውስጥ አሠራር በቴክኖሎጂ ከመደገፍ ባለፈ፣ የሌሎች ተቋማትን አቅም በመገንባት የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ስትራቴጂ እንዲሳካ በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የመቅደላ አምባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ካሳ ሻውል(ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ዲጂታል ቴክኖሎጂ የሀገር እድገት መሠረት በመሆኑ ዩኒቨርሲቲው ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫው አድርጎታል ብለዋል። በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማቶችን በማሟላት አገልግሎቱን ማዘመን መቻሉንና ሂደቱን በጥናትና ምርምር እያገዙ እንደሚገኙም ገልጸዋል። በመድረኩ ከወሎ፣ ከመቅደላ አምባ፣ ከወልድያ፣ ከራያ እና ከሰመራ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲሁም ከፌዴራል ተቋማት የተውጣጡ ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በኦሮሚያ ክልል የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች የሚመልሱ ተግባራት ተጠናክረው ቀጥለዋል
Apr 4, 2026 135
ጅማ፤ መጋቢት 26/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ለህዝቡ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጡ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ ነመራ ቡሊ ገለጹ። በጅማ ዞን ኦሞ ናዳ ወረዳ አሰንዳቦ ከተማ፣ በወረዳ ደረጃ የመጀመሪያ የሆነውን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። አቶ ነመራ ቡሊ በዕለቱ ባስተላለፉት መልዕክት፣ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በክልሉ በስፋት እየተተገበረ መሆኑንና የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በሂደት ለመመለስ እየተከናወነ ያለ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። አገልግሎቱ ብልሹ አሰራሮችን ከማስቀረት ባለፈ፣ የህዝቡን ጥያቄዎች አንድ በአንድ እየመለስን ለመሆናችን ማሳያ ነው ያሉት ኃላፊው፣ ወደፊትም አገልግሎቱን በማዘመን ለበርካታ ዜጎች ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የጅማ ዞን አስተዳዳሪ ቲጃኒ ናስር በበኩላቸው፣ የዞኑ ነዋሪዎች በተደጋጋሚ የሚያነሷቸውን የልማትና የአገልግሎት አሰጣጥ ጥያቄዎችን ለመፍታት መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በወረዳ ደረጃ እየተስፋፋ መሆኑን ገልጸዋል። የአሰንዳቦ ከተማ አስተዳዳሪ ነዚፍ ሼህ ከማል በማዕከሉ 11 ተቋማት 52 ዓይነት አገልግሎቶች በ8 መስኮቶች እንደሚሰጥ ጠቅሰው ባለሙያዎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ስልጠና ወስደው ወደ ስራ ገብተዋል ብለዋል።
የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) የጤና ሥርዓቱን የሚያዘምን አበረታች ውጤት እያስገኘ ነው
Apr 3, 2026 171
አዲስ አበባ፤መጋቢት 25/2018(ኢዜአ)፦የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) የጤና ሥርዓቱን የሚያዘምን አበረታች ውጤት እያስገኘ መሆኑን የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ ገለጹ። በጤና ሚኒስቴር ብሔራዊ የጤና ኢኖቬሽን ማበልፀግያና በሀርቫርድ ጤና ስርዓት ኢኖቬሽን ሃካቶን ትብብር በአዲስ አበባ የተዘጋጀው የ2026 ዓለም አቀፍ የጤና ኢኖቬሽን ጉባኤ መካሄድ ጀምሯል። ጉባዔው በኢትዮጵያ ለመጀመርያ ጊዜ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ7ኛ ጊዜ የሚካሄድ ሲሆን "ሰው ሰራሽ አስተውሎት፤ ለላቀ የጤና ሥርዓት ግንባታ" በሚል መሪ ቃል ከዛሬ መጋቢት 25 እስከ 26/2018 ዓ.ም ይቆያል። በዚሁ ጊዜ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ፤ የኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት የጤና ጥራትና ፍትሐዊ ተደራሽነትን በማጠናከር ከፍተኛ እገዛ እያደረገ ነው ብለዋል። በዲጂታል ዘርፍ የተወሰዱ የሕግና የአሰራር ማሻሻያዎችም የኢትዮጵያን የጤና ሥርዓት በማዘመን ተጨባጭ ውጤቶች ማስገኘታቸውን ገልጸዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መነሻነትም ሀገር በቀል የፈጠራ ክህሎትን በማዳበር የጤና ተቋማትን የማዘመን ሥራ ትኩረት እንደተሰጠው አስረድተዋል። በጤና ሚኒስቴር የዲጂታል ፈጠራ አስቻይ ምኅዳርም የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ መዋቅራዊ የአሰራር ለውጥ እየተደረገ እንደሚገኝ አንስተዋል። በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) ዘርፍ የጤና ሥርዓቱን ለማዘመን የሚከናወኑ ተግባራት ውጤታማነትን በማሳደግ ወሳኝ አቅም እየተፈጠረ መሆኑን ጠቅሰዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የዲጂታል ምኅዳሩን በማስፋት በዕውቀትና ክህሎት የበለጸገ የሰው ሃብት የማፍራት ስራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያን የጤና ሥርዓት ለማዘመን በሚደረገው ጥረት የሰው ሰራሽ አስተውሎትን ጥቅም ላይ በማዋል የአገልግሎት ጥራትን በማስጠበቅ የሰውን ህይወት ለመታደግ ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። በሀገራዊ ለውጡ ማግስት በዲጂታል ዘርፍ የተመዘገቡ አስደናቂ የዲጂታል ስኬቶችም ኢትዮጵያ ጉባኤውን ለመጀመሪያ ጊዜ እንድታዘጋጅ ማስቻሉን አስረተድዋል። በጉባኤው ላይ 60 ኢትዮጵያዊያን የጤና ሙያተኞች፣ የሶፍትዌር አልሚዎች፣ ተመራማሪዎችና ተማሪዎች የጤና ሥርዓትን የሚያሻሽሉ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ለውድድር እንደሚያቀርቡም አስታውቀዋል። በቀጣይም የዲጂታል መሰረተ ልማትን በማስፋት የፈጠራና ክህሎት ዝንባሌ ያላቸው ዜጎችን የማብቃት ሥራ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
የሲዳማ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ለመልካም አስተዳደር ችግሮች መፍትሔ እየሰጠ ነው
Apr 2, 2026 171
ሃዋሳ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦ የሲዳማ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ለመልካም አስተዳደር ችግሮች መፍትሄ እየሰጠ መሆኑን የይርጋለም ከተማ ተገልጋዮች ገለጹ፡፡ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቴክኖሎጂ የተለያዩ የመንግሥት ተቋማትን አገልግሎቶች በአንድ ዲጂታል ሥርዓት በማቀናጀት፣ ደንበኞች እንደ መንጃ ፈቃድ፣ መታወቂያ እና የባንክ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ በቀላሉ እንዲያገኙ ያስችላል። በሲዳማ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎትም 17 ተቋማት የገቡ ሲሆን ከ74 በላይ አገልግሎቶች እየተሰጡ መሆኑም ተመላክቷል፡፡ የማእከሉ ተገልጋዮች ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በቴክኖሎጂ የታገዘው የማእከሉ አገልግሎት ጊዜ፣ ወጪንና እንግልት የቀነሰና ለመልካም አስተዳደር ችግሮች መፍትሄን የሰጠ ነው፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል የይርጋለም ከተማ ነዋሪው አቶ ከበደ አመሎ የመጡበትን ጉዳይ በአስር ደቂቃ ውስጥ መፈጸማቸውን ጠቅሰው ከዚህ ቀደም የነበረው አሰራር የተንዛዛ እንደነበረ አስታውሰዋል፡፡ አገልግሎቱ በዲጂታል የታገዘ መሆኑና የተለያዩ ተቋማት በአንድ ቦታ መገኘታቸው የተገልጋዩን እንግልት ለመቀነስና ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ ማስቻሉን ተናግረዋል፡፡ የማእከሉ አገልግሎት የተገልጋይ እርካታን ከማሳደግ ባለፈ ሀገራዊ ፋይዳው ከፍተኛ መሆኑን የጠቀሱት አስተያየት ሰጪው የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመፍታት በመንግስትና ህዝብ መካከልም መተማመን ይፈጥራል ነው ያሉት፡፡ ሌላኛው ተገልጋይ አቶ ዎማ ጋቢሶ በበኩላቸው ውክልና ለመስጠት ወደ ማእከሉ መምጣታቸውን ጠቅሰው በተቋሙ የተፈጠረው አዲስ የስራ እሳቤ የተገልጋዩን ጊዜ፣ ወጪና እንግልት ከመቀነስ ባለፈ በእውቀት እንዲገለገል አስችሏል ብለዋል፡፡ ስለሚያገኙት አገልግሎት የህግ ድጋፍ ጭምር ማግኘታቸውን ጠቅሰው አገልግሎቱ በቴክኖሎጂ የታገዘ መሆኑና የተለያዩ ተቋማት በአንድ ላይ መኖራቸው አገልግሎቱን ቀልጣፋ እንዳደረገው ተናግረዋል፡፡ በማእከሉ የሚሰጠው አገልግሎት ፍትሃዊና ከዚህ ቀደም ለሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮች መፍትሄን ያመላከተ በመሆኑ ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በማእከሉ የሚሰጠው አገልግሎት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ በመሆኑ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘታቸውን የገለጹት ወይዘሮ መታሰቢያ አለማየሁ በበኩላቸው በአገልግሎት አሰጣጡ ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የማእከሉ መከፈት ከዚህ ቀደም ረጅም ጊዜ ወስዶ ይሰጥ የነበረውን አገልግሎት በ15 ደቂቃ ውስጥ መፈጸም በመቻላቸው ጊዜ፣ ወጪና እንግልትን ቀንሶላቸዋል፡፡ የሲዳማ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ እንግዳየሁ ዘውዴ በማእከሉ 17 ተቋማት መኖራቸውንና 74 አገልግሎቶች እየተሰጡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እስካሁን ከ35 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች አገልግሎት መሰጠቱን የጠቀሱት ዳይሬክተሩ የተገልጋዮች እርካታን ለመፈተሽ በተደረገው የዳሰሳ ጥናት ተግባሩ ውጤታማ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ከዚህ ቀደም በአገልግሎቱ ዘርፍ የሚታዩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመቅረፍ በመንግስትና ህዝብ መካከል መተማመን እንዲፈጠር እያስቻለ ነው ብለዋል፡፡ በቀጣይም በክልሉ በሚገኙ ሰባት ከተማ አስተዳደሮችና በሃዋሳ ከተማ ተጨማሪ ማዕከል በማቋቋም አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ እቅድ ተነድፎ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የሲዳማ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት መስከረም 15/2018 ዓ.ም ተመርቆ በይፋ ወደ አገልግሎት መግባቱ ይታወቃል፡፡
የሀገራዊ ለውጡ ትሩፋት የሆነው መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግስት አገልግሎት ስርነቀል ለውጥ እያመጣ ነው
Apr 1, 2026 595
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 23/2018(ኢዜአ)፦ የሀገራዊ ለውጡ ትሩፋት የሆነው መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግስት አገልግሎት ስርነቀል ለውጥ እያመጣ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። በመዲናዋ አምስተኛው የአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግስት አገልግሎት የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ቅርንጫፍ ስራ ማስጀመርያ መርሃ-ግብር ተካሂዷል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ መንግስት በመዲናዋ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶችን በፍጥነት በማጠናቀቅ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል። የዚሁ አካል የሆነውና የተገልጋዩን እንግልት በመቀነስ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አገልግሎት የሚሰጠው ማዕከል ለአገልግሎት በመብቃቱ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ሀገራዊ ለውጡ የመንግሥትን አሠራር ስርነቀል በሆነ መልኩ ለቀየረው መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግስት አገልግሎት ስኬትና ሌሎቹም ውጤታማ ተግባራት ዋነኛው ምንጭ ነው ብለዋል፡፡ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግስት አገልግሎት የሀገራዊ ለውጡ ትሩፋት መሆኑንም ጨምረው ገልፀዋል። ማዕከሉ የተለያዩ የመንግሥት አገልግሎቶችን በአንድ ስፍራ አቀናጅቶ ጊዜን፣ ወጪን፣ ጉልበትን በመቆጠብ እና እንግልትን በማስቀረት ፈጣንና ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ነው ብለዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በተለይ ተመጋጋቢ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማትን በአንድ ማዕከል በማሰባሰብ ዘመናዊ፣ ፍትሃዊና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ብልሹ አሰራሮችን ማስወገድ የሚያስችል እንደሆነም ተናግረዋል። በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ አብዛኛው ነዋሪ በንግድ ስራ ላይ የተሰማራ መሆኑን አስታውሰው፤ የሚያጋጥማቸወን እንግልት በማስቀረት ፈጣን አገልግሎት በመስጠት ውጤታማ እንዲሆኑ ያስችላል ነው ያሉት። አገልግሎቱ በብቁ የሰው ሀይል የተደራጀና ዘመኑን በሚመጥን አስተሳሰብና በላቀ የስራ ተነሳሽነት እንዲሁም በቴክኖሎጂ ለማገልገል መገንባቱን ገልጸዋል። አገልግሎቱ ለመዲናዋ ነዋሪዎች ብቻ ሳይሆን አዲስ አበባ የአፍሪካ መዲና እና የዲፕሎማሲ ማዕከል እንደመሆኗ በርካታ ስብሰባዎችን ለመታደም የሚመጡ አካላትና ቱሪስቶች ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ በሚያስችል ሁኔታ መሰራቱንም ጠቁመዋል።