ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
አውደ ጥናቱ ለኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ኃይል ልማት ቀጣይ ስራዎች መደላድል የሚሆን ግንዛቤ ተፈጥሮበታል
Dec 11, 2025 23
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦አውደ ጥናቱ ለኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ኃይል ልማት ቀጣይ ስራዎች መደላድል የሚሆን ግንዛቤ የተፈጠረበት መሆኑን የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ገለጸ። የመጀመሪያው ብሔራዊ የኒውክሊየር ኃይል መርሃ ግብር ሚና እና ኃላፊነት የተቋም ትግበራ አውደ ጥናት ምክክር መድረክ ዛሬ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ተሊላ በዚሁ ወቅት፥ የኒውክሊየር ኃይል ለኢነርጂ፣ ለግብርና፣ ለጤና እንዲሁም ለኢንዱስትሪ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ገለጸዋል። የዚህ ኃይል አጠቃቀም በዓለም አቀፍ ሕግ የሚመራ መሆኑን ገልጸው ሀገራት ሊከተሏቸወ የሚገቡ ቅደም ተከተሎች መኖራቸውን ጠቁመዋል። በአውደ ጥናቱ በሀገር ውስጥ ያሉ ባለድርሻ አካላት እና የሚመለከታቸው ሌሎች ተቋማት መሳተፋቸውንና ግንዛቤ መፈጠሩን ተናግረዋል። የኒውክሊየር ፕሮግራሙ ሀገራዊ ፕሮጀከት በመሆኑ ህብረተሰቡ ለስኬቱ የሚጠበቅበትን ሚና እንዲወጣ ማስቻል ላይ ውይይቶች መደረጋቸውን ጠቁመዋል። በአውደ ጥናቱ በዓለም አቀፍ የሕግ ማእቀፎች እና ሊከናወኑ በሚገባቸው ስራዎች ላይ ውይይት መደረጉንም አመላክተዋል። የተቋማት አቅም እና የሰው ኃይል ግንባታ ሌላኛው በአውደ ጥናቱ በስፋት የተዳሰሰ መሆኑን ጠቁመዋል። አውደጥናቱ በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት ቀጣይ ስራዎች መደላድል የሚሆን ግንዛቤ የተፈጠረበት መሆኑን ገልጸዋል። በአውደ ጥናቱ ከተሳተፉት መካከል የውመን ኢን ኒውክሊየር ኢትዮጵያ ፕሬዝደንት አበባ ጌጡ፤ አውደ ጥናቱ በቂ ግንዛቤ ያገኙበት መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የዓለም አቀፉ አቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ባስቀመጣቸው አቅጣጫዎች ላይ ግንዛቤ ማግኘታቸውን ነው የገለጹት። በቀጣይም በፕሮግራሙ ላይ የሴቶች አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንዲሆን በስልጠና እንዲሁም በተለያዩ አውደ ጥናቶች የማብቃት ስራ እንደሚሰራ አስታውቀዋል። በአውደ ጥናቱ ጥልቅ እውቀት ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ በኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ባለስልጣን የጨረራና ኒውክሊየር ቴክኖሎጂ የማሳወቅ እና ፈቃድ አሰጣጥ መሪ ስራ አስፈጻሚ ስሩር ከድር ናቸው። ተጨማሪ እውቀት በመፍጠር በዘርፉ የተሰማሩትን ለበለጠ ስራ የሚያነሳሳ መሆኑን ተናግረዋል።
ፋይዳ መታወቂያ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው -ተቋማት
Dec 11, 2025 94
ሐረር፤ ታህሳስ 2/2018 (ኢዜአ) ፡- ፋይዳ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን በሐረሪ ክልል የሚገኙ የተለያዩ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ገለጹ። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ እየተከናወኑ ከሚገኙ ተግባራት መካከል የመንግስት የአገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታላይዝ ማድረግ አንዱ ነው። ለዚህም ይረዳ ዘንድ ማንኛውም አገልግሎት ፈላጊ ዜጋ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያን እንዲይዝ መንግስት የተለያዩ አማራጮችን መዘርጋቱ የዚሁ ጥረት አካል ነው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የሐረሪ ክልል አገልግሎት ሰጪ ተቋማት፤ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በሐረሪ ክልል ጠቅላይ ዐቃቢ ህግ የውልና ማስረጃ ምዝገባ ጽሕፈት ቤት ባለሙያ አቶ ዘኪ አብዱልማሊክ ፤ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተግባራዊ መደረጉ በተለይም ከዚህ በፊት በመታወቂያ ረገድ ይስተዋል የነበረው ማጭበርበር ችግር ማቃለሉን ገልጸዋል። ፋይዳ ከሲስተም ጋር የተሳሰረ በመሆኑ አንድ ሰው በአንድ ማንነትና በአንድ መታወቂያብቻ እንዲገለገል አድርጓል፣ የነበሩ ብልሹ አሠራሮችንም ሙሉ በሙሉ እንዳሰቀረ ተናግረዋል። የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ሁሉንም ዜጎች ተደራሽ ያደረገ ነው ያሉት ደግሞ በሐረሪ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል ኢትዮ- ፖስታ በሚሰጠው አገልግሎት የካውንተር ባለሙያ አቶ አብዲሳ ተካ ናቸው። በተጨማሪም ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ ለግለሰብም ሆነ ለሀገር ደሕንነት የጎላ ፋይዳ እንዳለውና እንደ ሀገር ለተጀመረው የዲጂታላይዜሽን ሥራዎች አንዱ ማሳያ መሆኑንም አክለዋል። ሌላው በሐረሪ መሶብ የአንድ ማዕከል ኢትዮ-ፖስታ በሚሰጠው አገልግሎት የካውንተር ባለሙያ ዮሐንስ እስቂያስ በበኩላቸው፤ ፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ተቋማት ያለ ልዩነት አገልግሎት እንዲሰጡ ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ሲል ተናግረዋል። በአገልግሎት ሰጪ እና ተቀባዩ መካከልም መተማመን እንዲፈጠር ያስቻለ ስለመሆኑም አንስተዋል። የሐረሪ ክልል ወሳኝ ኩነት ምዝገባ ኤጀንሲ ኃላፊና የፋይዳ ብሔራዊ መታወቂያ አስተባባሪ አቶ አርሰላን አብዲ ፤ በክልሉ እስካሁን 263ሺህ ዜጎች የፋይዳ መታወቂያ ተመዝግበው መውሰዳቸውንና ይህም ከእቅዱ በላይ ማሳካት መቻሉን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በክልሉ የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ያልወሰዱ ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም አክለዋል። የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም እንደ ሀገር ለተጀመሩ የዲጂታላይዜሽን፣ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና ዲጂታል ኢኮኖሚ ስርዓት ግንባታ ፋይዳው የጎላ መሆኑን አስረድተዋል። የሀገር እና ዜጎችን ደሕንነትን በማስጠበቅ ረገድ ጉልህ አአስተዋጽኦ አለው ያሉት ሃላፊው፤ ዜጎች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ መያዝ እንደሚጠቅማቸው በመረዳት የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል።
የኢትዮጵያ የዲጂታል ክፍያ ስርዓት የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር በምሳሌነት የሚወሰድ ነው
Dec 11, 2025 65
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የዲጂታል ክፍያ ስርዓት የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር በምሳሌነት የሚወሰድ መሆኑን የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ዋና ጸኃፊ ዋምኬሌ ሜኔ ገለጹ፡፡ የአፍሪካ ሀገራትን የዕርስ በእርስ የንግድ ልውውጥ ለማሳለጥ የጋራ መገበያያ ገንዘብን ሥራ ላይ ማዋል እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል። ሁለተኛው የኢትዮጵያ የዲጂታል ክፍያ ዓመታዊ ጉበዔ ተካሂዷል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ዋና ጸኃፊ ዋምኬሌ ሜኔ በጉባዔው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በአፍሪካ በየዓመቱ የሚፈጸመውን የአምስት ቢሊዮን ዶላር የእርስ በእርስ የንግድ ልውውጥ በማሳለጥም የአህጉሪቱን የጋራ መገበያያ ገንዘብ ግብ ለማሳካት ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አስረድተዋል። የአህጉሪቱ የንግድ ልውውጥ በሶስተኛ ወገን ገንዘብ ይፈጸማል ያሉት ዋና ጸኃፊው፤ ይህም አፍሪካውያን ለአላስፈላጊ ወጪ እንዲጋለጡ እያደረጋቸው መሆኑን ገልጸዋል። የአፍሪካ ሀገራትን የዕርስ በዕርስ የንግድ ልውውጥ ወጪ ቆጣቢ፣ ዘመናዊና ፈጣን ለማድረግም አህጉራዊ የጋራ መጠቀሚያ ገንዘብን በሥራ ላይ ማዋል እንደሚገባ አስረድተዋል። በአህጉሪቱ የንግድ ልውውጥም ሀገራት በየራሳቸው ገንዘብ ግብይት የሚፈጽሙበትን ቀልጣፋ የአሰራር ሥርዓት መዘርጋት እንደሚገባም አብራርተዋል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናም የአፍሪካ ሀገራትን የንግድ ልውውጥ የሚያሳልጥ የአሰራር ሥርዓት ምክረ ሃሳቦችን በመፍጠር የድርሻውን እየተወጣ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ዋና ጸሃፊው ኢትዮጵያ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስኬታማ ስራ እየሰራች መሆኑንም ጠቁመዋል። በዲጂታል ክፍያ ስርዓት ፍትሐዊ የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር በምሳሌነት የሚወሰድ ሥራ እየሰራች መሆኗን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ መርሃ ግብር ለዲጂታል ሥርዓት ግንባታ ገንቢ ሚና እየተጫወተ ነው
Dec 11, 2025 71
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ መርሃ ግብር በህዝብና ተቋማት መካከል መተማመን በመፍጠር ለዲጂታል ሥርዓት ግንባታ ገንቢ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም አስታወቀ። የፕሮግራሙን ተቋማዊ አሰራርና ውጤታማነት ለማሳደግ የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ በአዋጅ 1284/2015 በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጸድቆ ወደ ስራ መግባቱ ይታወቃል። አዋጁ ነዋሪዎች የመታወቅ መብታቸው እንዲረጋገጥ፣ ሌሎች መብቶቻቸውን የመጠቀም እድላቸውን ለማስፋት፤ በአገልግሎት ሰጭና ተቀባይ መካከል በሚኖር ግንኙነት እምነት እንዲዳብር፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና የተሳለጠ አሰራር ለመዘርጋት ያለመ ነው። በብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የባለድርሻ አካላትና የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ሳሚናስ ሰይፉ ለኢዜአ እንደተናገሩት ዲጂታል ኢትዮጵያን በማሳለጥ ማጭበርበርን ከማስቀረት በተጨማሪ በህዝብና በተቋማት መካከል መተማመንን ለመፍጠር ዲጂታል መታወቂያ ጉልህ ሚና አለው። የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ አጀንዳና በዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ 2030 ውስጥ አንዱና ዋናው አስቻይ ምሰሶ መሆኑን ተናግረዋል። ለተለያዩ ዘርፎች አገልግሎት ለመስጠት አስቻይ ሁኔታን መፍጠር፤ ተደራሽነትን ማረጋገጥ እና ለዲጂታል የህዝብ መሰረተ ልማት መሰረት በመጣል በኢትዮጵያ ዲጂታላይዜሽንን ለማሳካት ጉልህ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። እስካሁን የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ያደረጉ ሰዎች ቁጥር 29 ሚሊየን መድረሱንም ጠቅሰዋል። በፕሮግራሙ የተቀመጠውን ቅድመ ሁኔታ ለሚያሟሉ ነዋሪዎች ባለ 12 አሃዝ ልዩ የፋይዳ መለያ ቁጥር እየተሰጠ እንደሚገኝና ይህ መለያ ቁጥር ያላቸው ሰዎች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ተደርገው እንደሚቆጠሩ አስረድተዋል። በምዝገባ ሂደቱ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ህዝቡ በንቃት እንዲሳተፍን ጥሪ አቅርበዋል። የዲጂታል መታወቂያ ከተቋማት ጋር መተሳሰሩ የአገልግሎቱን ተጠቃሚ ቁጥር ለማሳደግ ፋይዳ እንዳለው አመልክተዋል።
በኦሮሚያ ክልል ከ900 ሺህ በላይ ዜጎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ወስደዋል
Dec 11, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል 956 ሺህ ዜጎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸውን የክልሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን አስታወቀ። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ እየተከናወኑ ከሚገኙ ተግባራት መካከል የመንግስት የአገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታላይዝ ማድረግ አንዱ ነው። ለዚህም ይረዳ ዘንድ ከመደበኛው የቴክኖሎጂ ትምህርቶች በተጨማሪ የኢትዮ-ኮደርስ እና የመሳሰሉ የበየነ መረብ የክህሎት ስልጠናዎችን መንግስት እንደ አማራጭ ለዜጎች ምቹ ማድረጉ የዚሁ ጥረት አካል ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በተጀመረውና ለ5 ሚሊዮን ዜጎች የተመቻቸው የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና በሁሉም ክልሎች በተለያዩ ዙሮች እየተሰጠ ይገኛል። በኦሮሚያ ክልልም ስልጠናው ከተጀመረ ወዲህ ከ900 ሺህ በላይ ዜጎች የእድሉ ተጠቃሚ በመሆን በርካቶቹ በዘርፉ ሥራ እስከ መፍጠር መድረሳቸው ተገልጿል። የክልሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ጅማ ቱሉ ለኢዜአ እንደተናገሩት በክልሉ የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠናው ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተለያዩ ስራዎች ተሰርተዋል። የስልጠናው ዓላማ ዜጎች በዲጂታል ዘርፍ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ከማድረግ ባለፈ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚያግዛቸው ጠቁመዋል። በተጨማሪም ስልጠናው ተማሪዎች ከቴክኖሎጂ ጋር ያላቸው ግንኙነት የጠበቀ እንዲሆን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ሲሆን ለስራ ፈላጊዎች ደግሞ እድላቸውን የሚያሰፋ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና እቅዱን ለማሳካት የግንዛቤ ፈጠራ፣ ቤተ ሙከራዎች የማዘጋጀት፣ ኮምፒዩተሮችና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን የማሟላት እንዲሁም የስልጠና ማዕከላትንና ሌሎችንም የማመቻቸት ስራዎች በሰፊው መሰራታቸውን ገልጸዋል። በክልሉ ዞኖችና ከተሞች ለመንግስት ሰራተኞች፣ ነጋዴዎች፣ ለአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች፣ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች የተመረቁ ተማሪዎች በስልጠናው በንቃት እየተሳተፉ ይገኛሉ ብለዋል። በአጠቃላይ በክልሉ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዜጎችን የስልጠናው ተጠቃሚ ለማድረግ የታቀደ ሲሆን እስካሁን 956 ሺህ ዜጎች ስልጠናውን መውሰዳቸውን ገልጸዋል። በብሔራዊ መታወቂያ የምዝገባ ስራ ላይ በርካታ ሰልጣኞች በቀጥታ ተሳታፊ በመሆን የስራ እድል ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኙም አብራርተዋል። በተያዘው በጀት አመት በክልሉ በኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና የተቀመጠውን ዕቅድ ለማሳካት ርብርቡ እንደሚቀጥልም ኢንጂነር ጅማ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በዲጂታል ክፍያ ያስመዘገበችው አስደናቂ ስኬት ተጨማሪ ግቦችን ለማሳካት መሠረት የሚሆኑ ናቸው
Dec 10, 2025 132
አዲስ አበባ፤ታኅሣስ 1/2018(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በዲጂታል ክፍያ ያስመዘገበችው አስደናቂ ስኬት ተጨማሪ ግቦችን ለማሳካት መሠረት የሚሆኑ ናቸው ሲሉ የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ። ሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ በስኬት ተጠናቋል። በጉባኤው ማጠናቀቂያ ንግግር ያደረጉት የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በዲጂታል ክፍያ ዘርፍ እያስመዘገበች ያለችው ዕድገት አስደናቂ ነው። አሁን ላይ አብዛኛው ዜጋ ከፍተኛ መጠን ያለው ጥሬ ገንዘብ መያዝ አቁሟል ያሉት ገዥው፤ ኢትዮጵያውያን የዲጂታላይዜሽን እና የዳታ ሽግግርን በፍጥነት እየተላመዱ እንደሚገኙም አስረድተዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት በተዘረጋው የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት በየዓመቱ ከ18 ነጥብ 5 ትሪሊዮን ብር በላይ የገንዘብ ዝውውር መከናወኑን ተናግረዋል። ይህን የገንዘብ ዝውውር በጥሬ ገንዘብ ቢከናወን ከፍተኛ ወጪና መጨናነቅ ይፈጥር እንደነበር ጠቁመው፤ ይህ ስኬት ከጥቂት ዓመታት በፊት ፈጽሞ የማይታሰብ እንደነበር ጠቅሰዋል። የመሠረተ ልማትን ለማስፋፋት የተሰጠው ትኩረት ዋነኛ የስኬቱ መገለጫ መሆኑን ገልጸዋል። መንግሥትን ወደ ዲጂታል ግብይት እና የገንዘብ ዝውውር አገልግሎት ለማሸጋገር የሰጠው ትኩረት ለተመዘገበው ውጤት ትልቅ እርምጃ መሆኑን ጠቅሰው፤ በትክክል የታሰበበት፣ በጥንቃቄ የተቀረጸና ተግባራዊ የተደረገ የስትራቴጂ ውጤት ስለመሆኑም ጠቁመዋል። እስካሁን የተገኘውን ውጤት ይበልጥ ለማጎልበት እንደሚሰራ ጠቁመው፤ ውጤቱ የሚያዘናጋ ሳይሆን መስፈንጠሪያ ሊሆን እንደሚገባም ተናግረዋል። በቀጣይ የዲጂታል ባንኪንግ ተጠቃሚዎችን እምነት ለማሳደግ እና የሥርዓቱን ደኅንነት ይበልጥ ለማረጋገጥ እንደሚሰራ ጠቅሰው፤ በገጠርና በከተማ ያለውን የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ልዩነት ለመቀነስ ይሠራል ብለዋል። እንዲሁም የፈጠራ ሥራዎችን በበቂ ሀብት የመደገፍ ሥራዎች ወሳኝ በመሆናቸው በልዩ ትኩረት ይሠራል ብለዋል። ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በቁርጠኝነት ሠርታ ያስመዘገበቻቸው ትላልቅ ውጤቶች በቀጣዮቹ ዓመታት ለማሳካት ያስቀመጠቻቸውን ግቦች ለማሳካት ትልቅ መሠረት የሚሆኑ ናቸውም ብለዋል። ኢትዮጵያ የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን ለመገንባት ትክክለኛ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በመቅረፅ ትክክለኛውን እርምጃ መውሰዷንም ገልጸዋል። ሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ የመረጃ መሠረተ ልማትን ለማጠናከር፣ የዲጂታል ክፍያ እና ሰፋፊ የዲጂታል ስትራቴጂዎችን ለማስገንዘብ ሰፊ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን ለማስፋፋት መንግስት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ለዚህም በርካታ ኢንቨስትመንት መከናወኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የዲጂታል ክፍያ ዘርፍ እንዲስፋፋ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይ ትኩረት ከሚሰጣቸው ተግባራት መካከል የመረጃ ሉዓላዊነት ጉዳይን አንስተዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በብዙ መልኩ ኢንቨስት እያደረገች እንደምትገኝም አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የዲጂታል ፋይናንስና የክፍያ ሥርዓት በፈጣን የዕድገት ጎዳና ላይ እንደምትገኝም ጠቁመዋል። ከ2026 -2030 የሚተገበረው ብሔራዊ የዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ በሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ መክፈቻ ላይ ይፋ መደረጉን ይታወቃል።
የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኅይል ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት ያለመ ነው
Dec 10, 2025 144
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር ከኢኮኖሚው ጋር አብሮ እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኅይል ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት ያለመ መሆኑን የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ተሊላ ገለጹ። የመጀመሪያው ብሔራዊ የኒውክሊየር ኃይል መርሃ ግብር ሚና እና ኃላፊነት የተቋም ትግበራ አውደ ጥናት የምክክር መድረክ ሁለተኛ ቀን ቀጥሏል። የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኅይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ተሊላ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኒውክሊየር ኃይል ተፈጥሮ ለአንድ ሀገር ዘላቂ ልማት እና እድገት ወሳኝ ነው። ኢትዮጵያ የምትከተለው አረንጓዴ ኢኮኖሚ መሆኑን ገልጸው፤ የኢንዱስትሪዎቿ ቁጥር እና ዓይነት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መሆኑን ገልጸው፤ ይህ ወደ ኋላ እንዳይመለስ የኃይል ምንጭን አስቀድሞ ማዘጋጀት ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎት ምላሽ መስጠት የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አብዱረዛቅ ኡመር በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ከአካባቢ ጥበቃ ጋር የተስማማ በቂ እና አስተማማኝ ኃይል ለኢንዱስትሪዎች በማቅረብ ወደ ፊት መራመድ እንደምትፈልግ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን ሰላማዊ የኒውክሌር ኃይል አማራጭ የሀገሪቱን የልማት ትልሞች የሚያሳካ መሆኑን ጠቁመዋል። በመካሄድ ላይ ባለው ዓውደ ጥናት የተለያዩ ሀገራት ልምድ እና ተሞክሮዎች ቀርበው ውይይት እየተደረገባቸው መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም አንድ ሰላማዊ የኒውክሊየር መሰረተ ልማት ለማቋቋም መከናወን ባለባቸው ተግባራት ላይ ግንዛቤ እየተፈጠረ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ከባንክ ስርዓት ጋር የማጣመር ሥራ በይፋ ተጀመረ
Dec 10, 2025 123
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ):- የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ከባንክ ስርዓት ጋር የማጣመር ሥራን ዛሬ በጋራ ማስጀመራቸውን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እና የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም አስታወቁ። ሁለቱ ተቋማት ባወጡት የጋራ መግለጫ ፋይዳ ዲጂታል የማንነት መረጃ ከሁሉም ባንኮች የደንበኞች ባንክ ሂሳብ ቁጥር ጋር የማጣመር (Harmonization) ስራን በይፋ መጀመሩን ገልጸዋል። ይህ የመረጃ ሥርዓቶችን የማጣመር ስራ ደንበኞች ባሉበት ቦታ ሆነው ደህንነቱ በተጠበቀ ሁኔታ ገንዘብ ማስተላለፍ እንዲችሉ፣ በሀሰተኛ ሰነድ የራሳቸውን ሂሳብ ሌሎች ማንቀሳቀስ እንዳይችሉ፣ በቀላሉ የብድር አገልግሎትን ማግኘት እንዲችሉ እና በአንድ ፋይዳ መታወቂያ የሁሉንም ባንክ ሂሳብ መጠቀም እንዲያስችላቸው ተመላክቷል። ባንኮች በዚህ መረጃ ጥምረት የደንበኞቻቸውን ትክክለኛ እና ወቅታዊ መረጃን እንዲያገኙ፣ በሀሰተኛ ማንነት የሚከሰት የገንዘብ መጭበርበርን ከመከላከል ባለፈ ለፋይናንስ ሴክተር ዲጂታል ትግበራ ቁልፍ የዲጂታል መሰረተ ልማት ሆኖ እንደሚያገለግል መግለጫው ያትታል። ይህን የባንክ ሂሳብ ቁጥር ከፋይዳ መረጃ ጋር ለማጣመር ደንበኞች ወደ ባንክ ቅርንጫፎቻቸው በአካል በመሔድ ወይም ኦንላይን(ባንኩ በሚያስቀምጠው አሰራር መሰረት) የፋይዳ ተለዋጭ ቁጥር (16 አሀዝ-FAN Number) በማቅረብ ማከናወን ይችላሉ። ደንበኞች በተጠቀሰው የጊዜ ገደብ ማለትም እስከ መጋቢት 30 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ የባንክ ሂሳባቸውን ከፋይዳ መረጃ ጋር እንዲያጣምሩ ብሔራዊ ባንክ አሳስቧል። ለፋይዳ ያልተመዘገበ ማንኛውም የባንክ ደንበኛ በቅድሚያ በአቅራቢያው በሚያገኘው የፋይዳ ምዝገባ ጣቢያ በመሄድ መመዝገብ እንዳለበትና ባንኮች በዚህ ሂደት ደንበኞች መጉላላት እንዳያጋጥማቸው አስፈላጊውን ቅድመ ሁኔታ በመፈፀም ላይ እንደሚገኙ ተገልጿል። በሁሉም ባንኮች አዲስ ሂሳብ መክፈት(New Account Opening) (በ “VeriFayda 2” እንዲጀመር፣ እንዲሁም ነባር ሂሳቦችን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር ማስተሳሰር (Existing Account Harmonization) ትግበራም በ “VeriFayda 2” ተግባራዊ የሚደረግበት የጊዜ ሰሌዳ ወጥቶ ለሁሉም ባንኮች ህዳር 25 ቀን 2018 ዓ.ም መሰራጨቱ በመግለጫው ላይ ሰፍሯል። ቀደም ሲል ሁሉም ባንኮች አዲስ ሂሳብ ለመክፈት የ VeriFayda 1 ስርዓትን ሲጠቀሙ መቆየታቸውም ተመላክቷል፡፡ ከዚህ በኋላ ባንኮች ይበልጥ ዘመናዊና የተቀናጀ ወደ ሆነ ስርዓት “VeriFayda 2” (በኢቲስዊች - EthSwitch በh-A eKYC Service) የማሸጋገር ሥራን በተሳካ ሁኔታ እንዲያከናውኑ የፕሮግራሙና የኢቲስዊች የቴክኖሎጂ ባለሙያዎች ለባንክ ተቋማት የቴክኒክ ድጋፍ እና ክትትል እያደረጉ ይገኛል። በቀጣይም የቴክኒክ ድጋፉ እንደሚቀጥል ባንኩ አስታውቋል። በተመሳሳይ ሁሉም ባንኮች ለደንበኞቻቸው አዲስ የባንክ ሂሳብ ለመክፈትም ሆነ ከነባር ሂሳብ ጋር የማጣመር ስራን በመስራት ከVeriFayda 1 (old eKYC) ሙሉ በሙሉ ወደ VeriFayda 2 (new eKYC Service) መሸጋገር እንደሚኖርባቸው ባንኩ አሳስቧል። ይህንን ተከትሎ ቀደም ሲል ባንኮች ሲጠቀሙበት የነበረው የ VeriFayda 1 (eKYC Service) ስርዓት አገልግሎት መስጠት እንደሚያቆምም አመልክቷል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክና የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ይህን የማጣመር ስራ በፍጥነት ወደ ትግበራ ማስገባታቸው ለፋይናንስ ዘርፉ ብቻ ሳይሆን ሀገሪቱ ወደ ትራንስፎርሜሽን በምታደርገው ጉዞ ላይ ትልቁን ሚና እንደሚጫወት ተመላክቷል።
የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ዝርያን ለማሻሻል የተጀመሩ ውጤታማ ተግባራት ይጠናከራሉ
Dec 10, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ዝርያን ለማሻሻል የተጀመሩ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዳኛቸው በየነ (ዶ/ር) ገለጹ። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በግብርናው ዘርፍ ያሉ እምቅ ሀብቶችን ጥቅም ላይ ለማዋል የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ሲሆን የእንስሳት ምርታማነትን ለማሳደግ የተሠሩ ስራዎችም ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በተለይም የሌማት ትሩፋት ተግባራዊ ከሆነ ወዲህ የእንስሳት ምርታማነት በተጨባጭ ያደገ ሲሆን የበርካቶችን ህይወት በመለወጥም ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጠ እንደሚገኝ ነው የተመላከተው፡፡ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዳኛቸው በየነ (ዶ/ር)፤ ኢንስቲትዩት የዳልጋ ከብቶችን ጨምሮ የእንስሳት ሃብቶች ላይ የዝርያ ማሻሻያዎችን በመሥራት የእንስሳት ተዋጽኦ አቅርቦት እንዲጨምር ትልቅ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ብለዋል፡፡ በተለይም ከፍተኛ ምርት መስጠት የሚችሉ የውጭ ዝርያዎችን በሀገር ውስጥ ካሉ ላሞችና ጊደሮች ጋር በማዳቀል የተሻሻሉ ዝርያ ያላቸው እንዲበራከቱ እያደረገ ይገኛል ብለዋል፡፡ ይህም አርብቶና አርሶ አደሩ የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎችን እንዲያገኙ በማድረግ ከእንስሳቱ የሚያገኙት ተዋጽኦ በመጠንና በጥራት እያደገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ለዚህም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተግባራዊ የተደረገው የሌማት ትሩፋት ዘርፉ ከፍተኛ ትኩረት እንዲያገኝ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ በቀጣይም በሰው ሰራሽ ዘዴ የማዳቀል፣ የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን የመጠቅምና ባለሙያዎች ተጨማሪ ክህሎት እንዲያገኙ የማድረግ ሥራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል፡፡ ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አያይዘውም፤ ኢንስቲትዩቱ የሚያመርተውን የፈሳሽ ናይትሮጂን ደህንነቱ ተጠብቆ ለእንስሳት ዝርያ ማሻሻያ ተግባር እንዲውል እየተደረገ መሆኑንም አክለዋል። ኢንስቲትዩቱ በበጀት ዓመቱ 4 ነጥብ 9 ሚሊዮን ላሞችና ጊደሮችን ለማዳቀል የተያዘውን ግብ ለማሳካት እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የሆለታ እንስሳት ልማት ማዕከል ኃላፊ አራርሳ ዱጉማ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ማዕከሉ ኢትዮጵያ በእንስሳት ዘርፉ ላይ ያላትን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎችን እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ዝርያዎችን የማሻሻል፣ የእንስሳት አዳቃይ ቴክኒሺያኖችን የማሰልጠንና የተቀነባበረ መኖ ማምረትን ጨምሮ ሌሎችንም ስራዎች እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ማዕከሉ የተሻሻሉ ጊደሮችን ለተጠቃሚዎች ተደራሽ በማድረግ ላይ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር ፈጣን የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ዕድገቷን ለማሳለጥ ወሳኝ ሚና ይኖረዋል
Dec 10, 2025 86
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር በአስተማማኝ የኃይል አቅርቦት ፈጣን የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ዕድገቷን ለማሳለጥ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ ገለጸ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በተመረቀበት ወቅት የ30 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ሜጋ ፕሮጀክቶችን ማብሰራቸው ይታወሳል። የጉባ ብስራት ከሆኑት ብሔራዊ ፕሮጀክቶች ውስጥም ግዙፍ የአየር ማረፊያ፣ አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ቤቶች፣ የአፈር ማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታና ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር ይገኙበታል። በኅዳር 29 ቀን 2018 ዓ.ም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) እና የባለድርሻ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት የኢትዮጵያን የኒውክሊየር ኃይል ልማት መርሃ ግብር ማስጀመሪያና የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ይፋዊ የሥራ ማስጀመሪያ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። በማስጀመሪያ መድረኩ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኢነርጂ ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ፣ የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሚካኤል ቹዳኮቭና የባለድርሻ ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዚሁ ወቅት በዓለም አቀፍ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ የቴክኒክ ትብብር መምሪያ የአፍሪካ ጉዳዮች ክፍል ዳይሬክተር ጋሻው ገበየሁ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ ከፍተኛ የህዝብ ቁጥር ያላትና ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እያስመዘገበች የምትገኝ ሀገር ናት። የኢትዮጵያን የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ልማት ለማፋጠንም አነስተኛ የካርቦን ልቀት ያለው አስተማማኝ የኒውክሊየር ኃይል አቅርቦት ወሳኝና ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል። የዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲም በቴክኒክ ትብብር አማካኝነት ለኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር አስፈላጊውን ድጋፍ ለመስጠት ቁርጠኛ መሆኑን ተናግረዋል። የኒውክሊየር ሳይንስና ቴክኖሎጂ በግብርና፣ ጤና፣ ኢንዱስትሪ፣ ውሃና በአካባቢ ጥበቃ አስተዳደር ሥርዓት የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማሳለጥ ወሳኝ መሳሪያ መሆኑን አንስተዋል። የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር በአስተማማኝ የኤሌክትሪክ የኃይል አቅርቦት በአነስተኛ የካርቦን ልቀት ለአካባቢ ሥነ-ምኅዳር ደኅንነት ተመራጭ መሆኑን አስረድተዋል። በኢትዮጵያም አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን በመፍጠር የግብርና፣ ኢንዱስትሪና ሌሎች የኢኮኖሚና ማህበራዊ መስኮች ቀጣይነት ያለው ዕድገት ለማሳለጥ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው አንስተዋል። በቀጣይም ኢትዮጵያ የኒውክሊየር ሳይንስና ቴክኖሎጂ ልማትን የሚያሳልጥ ብቁ ሰው ሃይል ማፍራት እንደሚኖርባት አስገንዝበዋል። የዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ ከኢትዮጵያ ጋር የሚኖረውን ትብብር አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
ማዕከሉ በምርምር የወጡ የተሻሻሉ የስንዴ ዝርያዎችን እያባዛ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ እያደረገ ነው
Dec 10, 2025 60
አዳማ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- የቁሉምሳ ግብርና ምርምር ማዕከል በምርምር የወጡ የተሻሻሉ የስንዴ ዝርያዎች እያባዛ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ እያደረገ እንደሚገኝ አስታወቀ። በምርምር የወጡ የስንዴ ዝርያዎች በሄክታር እስከ 72 ኩንታል ምርት የሚሰጡ እንደሆኑ ተመልክቷል። የምርምር ማዕከሉ ዳይሬክተር አቶ ሽመልስ አለማየሁ ለኢዜአ እንዳመለከቱት ፤ ማዕከሉ በሀገሪቱ የስንዴ ምርምር ብሔራዊ ማስተባበሪያ ሆኖ እየሰራ ይገኛል። "መልካ፣ ጉቱ፣ አስጎሪ፣ ዳካ" እና ሌላም ስያሜ የተሰጣቸው የተለያዩ የተሻሻሉ የስንዴ ዝርያዎችን በማባዛት ለአርሶ አደሩ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። በምርምር የወጡ የስንዴ ዝርያዎች ቢጫ ዋግና የስንዴ ራስ አድርቅ በሽታዎችን በመቋቋም ከተለመደው የስንዴ ዝርያ የበለጠ ከፍተኛ ምርት መስጠት እንደሚችሉ በምርምር ሂደት ማረጋገጣቸውን አስረድተዋል። የተሻሻሉት የስንዴ ዝርያዎች በማዕከሉ በሄክታር እስከ 72 ኩንታል፤ በአርሶ አደር ማሳ ደግሞ እስከ 61 ኩንታል በሄክታር መስጠት እንደሚችሉ አስረድተዋል። በማዕከሉ እስከ አሁንም 113 የስንዴ ዝርያዎች በምርምር በማውጣት ለተጠቃሚዎች ተደራሽ መደረጉን ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ ከወረር እና ከቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል ጋር በመተባበር 45 የማካሮኒ እና ፓስታ "ዱረም" የተሰኙ የስንዴ ዝርያዎች በምርምር ማውጣት መቻሉንም አንስተዋል። የቁሉምሳ ግብርና ምርምር ማዕከል የሚያወጣቸውን የተሻሻሉ የስንዴ ዝርያዎቸን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረጉን ተግባር አጠናክሮ መቀጠሉንም አስታውቀዋል። ሀገሪቱ በምግብ ራስን በመቻል የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ያስቀመጠችውን ግብ ለማሳካት ማዕከሉ ከሌሎች መሰል ተቋማት ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። በዚህም የምርምር ማዕከሉ በግብርና ዘርፍ እየተተገበሩ ያሉትን ኢኒሼቲቮችና የሽግግር ሂደቱን በግንባር ቀደምትነት በቴክኖሎጂና አዳዲስ አሰራር እያገዘ ይገኛል ነው ያሉት። በተጨማሪ ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ የስንዴ ዝርያዎችን በምርምር በማውጣት አባዝቶ መነሻ ዘር እያቀረበ እንደሚገኝም አብራርተዋል።
በክልሉ አገልግሎት አሰጣጥን የሚያሳልጡ የሪፎርም ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Dec 10, 2025 52
ባህር ዳር ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ቀልጣፋና ዘመኑን የሚመጥን ለማድረግ የሚያስችሉ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ሲቪል ሰርቪስና ሰው ሃብት ልማት ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የሪፎርም ድጋፍና ክትትል ዳይሬክተር አቶ እንዳላማው ይታይ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ከሃምሌ 2017 ዓ.ም ጀምሮ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን በቴክኖሎጂ የታገዘና ወቅቱን የሚመጥን እንዲሆን የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ነው። በሀገር አቀፍ ደረጃ የፀደቀውን የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ፖሊሲ መሰረት በማድረግ ከፌደራል መንግስቱ ተናባቢ በሆነ አግባብ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ግልጽና ቀልጣፋ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርሙ የህዝብን አገልግሎት የማግኘት ፍላጎት በሚያረካና ቅሬታዎችን ሊመልስ በሚችል መልኩ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። የአገልግሎት አሰጣጡ ቀልጣፋ፣ ግልጽ፣ ጊዜና ወጪ ቆጣቢ፣ ዲጂታላይዝድና ዘመኑን የሚመጥን መሆን እንደሚጠበቅበት ገልጸው፤ ይህንን ታሳቢ ያደረጉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ሪፎርሙ ብዝሃነትና አካታችነት ያለው፣ ነጻና ገለልተኛ እንዲሆን ጭምር ተደርጎ እየተሰራ ያለው። ሪፎርሙ ለተመደበበት ሙያ ብቁና ዲጂታላይዝድ የሆነ ሲቪል ሰርቫንት መፍጠርን መሰረት ያደረገ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ቅቡልነት ያለው የመንግስት ሰራተኛ እንዲኖር ያስችላል ብለዋል። ብቃት ያለው አመራር፣ ባለሙያና ተቋም በመፍጠር ተዓማኒነት ያለው አገልግሎትን መዘርጋት ግድ የሚልበት ጊዜ መሆኑን ገልጸው "መሶብ" የአንድ ማዕከል አገልግሎት የዚህ አንዱ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ከሪፎርም ስራዎች መካከል አንዱ "መሶብ" የአንድ ማዕከል አገልግሎት መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም በክልል ደረጃ እንዲሁም በባህር ዳርና ደሴ ከተማ አስተዳደሮች ተመርቆ ወደ ስራ መግባቱን ገልጸዋል። የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በቴክኖሎጂ የታገዘ፣ ግልጽና በርካታ ጉዳዮችን በአንድ ጊዜ እልባት የሚሰጥና ህብረተሰቡ ባለበት ቦታ ሆኖ ያለምንም እንግልት አገልግሎቱን እንዲያገኝ ያስቻለ የሪፎርሙ አካል ነው ብለዋል። በሌሎች አካባቢዎችም እስከ ወረዳ ድረስ ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑንም አረጋግጠዋል። የተጭበረበረ የትምህርት ማስረጃ ማጣራት፣ የባለሙያውን የአቅም ክፍተት በተለያዩ ስልጠናዎች ማብቃትና ተዓማኒና ግልጽ የሆነ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት የሪፎርሙ አካል መሆናቸውን ገልጸዋል። የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ሪፎርሙ ሦስት ዓመት የሚወስድ መሆኑን ጠቅሰው፤ በታቀደለት ጊዜ ለማጠናቀቅ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
የሳይበር ጥቃቶችን በመከላከል ብሔራዊ ጥቅምን የማስጠበቅ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል
Dec 10, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- በቁልፍ መሠረተ-ልማቶች ላይ የሚቃጡ ዓይነተ-ብዙ የሳይበር ጥቃት ሙከራዎችን በማክሸፍ ብሔራዊ ጥቅምን የማስጠበቅ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር(ኢመደአ) አስታወቀ። በአስተዳደሩ የሳይበር መከላከል ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር መሐመድ ፈረጃ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በያዝነው በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሦስት ወራት 13ሺህ 443 ጥቃቶችና የጥቃት ሙከራዎች ተመዝግበዋል። ከሙከራዎቹ መካከልም ከፍተኛውን መጠን የያዘው ‘ሰርጎ ገብ’ የተሰኘው የሳይበር ጥቃት መሆኑን ገልጸው፤ ይህም በድረ ገጽ፣ በቁልፍ መሠረተ-ልማቶች እና ሌሎች ዘርፎች ላይ ዒላማ ያደረጉ እንደነበርም አስረድተዋል። በመሆኑም በኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር እና ቁልፍ መሠረተ-ልማቶቹን በሚያሥተዳድሩ ተቋማት ጥረት 97 ነጥብ 16 በመቶ ለሚሆኑት የጥቃት ሙከራዎች ምላሽ ተሰጥቷል ብለዋል። በዚህም መሠረት የሳይበር ጥቃቶቹን በመቆጣጠር፣ የጉዳት መጠንን በመቀነስ፣ ድጋሚ ለጥቃት እንዳይጋለጡ ደኅንነታቸውን የማጠናከር ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል። የሳይበር ጥቃት ሙከራዎቹ ቢሳኩ እንደሀገር ይደርስ የነበረው ጉዳት ከፍተኛ መሆኑንም ነው አቶ መሐመድ ፈረጃ የተናገሩት። በኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር እና በቁልፍ መሠረተ-ልማቶቹ አሥተዳዳሪ ተቋማት የጋራ ጥረት በርካታ ጥቃቶችን መከላከል መቻሉን ጨምረው ገልጸዋል። በቀጣይም በሀገር ላይ የሚቃጡ የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል ቅንጅታዊ ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አመላክተዋል።
ኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ፕሮግራሟን ከዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ስታንዳርድና መመሪያዎች ጋር በተጣጣመ መልኩ ትተገብራለች
Dec 9, 2025 155
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018 (ኢዜአ):- ኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ፕሮግራሟን ከዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ስታንዳርድና መመሪያዎች ጋር በተጣጣመ መልኩ እንደምትተገብር ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ከዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር እና የኑክሌር ኢነርጂ ዲፓርትመንት ኃላፊ ሜካኤል ቹዳኮቭ (ዶ/ር) ጋር ዛሬ ተወያይተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፤ ከምክትል ዋና ዳይሬክተሩ ጋር ትብብርን በሚያጠናክሩ ስትራቴጂክ ጉዳዮች ላይ ፍሬያማ ውይይት መደረጉን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ኃይልና ቴክኖሎጂን ለንጹህ ኢነርጂ፣ ለጤና፣ ለግብርና፣ ለኢንዱስትሪና ለምርምር ልህቀት የመጠቀም ጽኑ መሻት እንዳላት አመልክተዋል። ለዚህም ሀገራዊ የኑክሌር ኃይል ፕሮግራምን በቅርቡ መጀመሯንና የኑክሌር ኃይል ኮሚሽንን በማቋቋምም በይፋ ወደ ሥራ መገባቱን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ፕሮግራሟን ከዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ስታንዳርድና መመሪያዎች ጋር በተጣጣመ መልኩ እንደምትተገብርም አረጋገጠዋል። ዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ኢትዮጵያ ከኑክሌር ኃይል ስትራቴጂካዊ ተጠቃሚነቷን ለማረጋገጥ የጀመረችውን ጉዞ እውን ለማድረግ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ እንደሚያደርግ ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ እንደገለጹላቸውም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የኒውክሌር ልማት ከአየር ንብረት ጋር የተጣጣመ ጠንካራ ኢኮኖሚ ሥርዓት የመገንባት ርዕይን ያነገበ ነው
Dec 9, 2025 144
አዲስ አበባ፤ ህዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ልማት ከአየር ንብረት ጋር የተጣጣመ በአስተማማኝ የኃይል አቅርቦት የተመሠረተ ጠንካራ የኢኮኖሚ ሥርዓት የመገንባት ርዕይን ያነገበ መሆኑን የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ ገለጹ። የመጀመሪያው ብሔራዊ የኒውክሌር ኃይል መርሃ ግብር ሚናና ኃላፊነት የተቋም ትግበራ አውደ ጥናት የምክክር መድረክ መካሄድ ጀምሯል። ከዛሬ ኅዳር 30 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለሶስት ቀናት በሚቆየው የአውደ ጥናት መድረክ የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ፣ የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሚካኤል ቹዳኮቭና የባለድርሻ ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ አስተማማኝ፣ ተዓማኒነትና ሰላማዊ የኒውክሌር መርሃ ግብር ለመገንባት ቁልፍ እርምጃ ጀምራለች። የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ልማት ከአየር ንብረት ጋር የተጣጣመ ጠንካራ የኢኮኖሚ ሥርዓት የሚገነባ አስተማማኝ የኃይል አቅርበት መፍጠርን ርዕይ ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የኒውክሌር ኃይል ልማት ሥራም ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና የህዝብ ቁጥርን ታሳቢ በማድረግ በኃላፊነት፣ ግልጽነትና ከዓለም አቀፍ የደኅንነት ጥበቃና ደረጃዎች ጋር ተጣጥሞ የሚተገበር መሆኑን ተናግረዋል። በዓለም አቀፍ አቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ እና በባለድርሻ አካላት ጋር በሚደረግ ጠንካራ ትብብር የተመሠረተ አጋርነት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ልማት የጤና፣ ግብርና፣ ኢንዱስትሪ ሳይንስና ምርምር ዘርፎችን ተወዳዳሪነት የሚያልቅ ብሔራዊ ፕሮጀክት ነው ብለዋል። የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሚካኤል ቹዳኮቭ፤ የኢትዮጵያ የኒውክሌር ልማት ለአፍሪካና ዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ወሳኝ ወደ ፊት የመራመድ ምልክት እንደሆነም ገልጸዋል። ይህም የኢትዮጵያን የረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ልማትና ብልጽግና የሚደግፍ ንጹህ፣ አስተማማኝና ዘላቂ የኃይል ደኅንነትን ለማስጠበቅ ስትራቴጂያዊ ምልክት ተደርጎ እንደሚወሰድ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የኒውክሌር ልማት ርዕይም ከህዝቧ የዕድገት ምኞት ባለፈ ከአፍሪካ የመለወጥ ህልም ጋር የተጣጣመ መሆኑን አስታውቀዋል። በርካታ ሀገራትም ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር የተጣጣመ ዕድገትን ለማስቀጠል የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎትና ደኅንነትን የሚያጠናክር የኒውክሌር ኃይል መርሃ ግብሮችን እየመረመሩ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያን የኒውክሌር ልማት መርሃ ግብር ደህንነት፣ አስተማማኝነትና ዘላቂነትም ከሀገራዊ ራዕይ ጋር የተጣጣመ እንዲሆን የሚያደርጉትን ትብብር አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ የቴክኒክ ትብብር መምሪያ የአፍሪካ ጉዳዮች ክፍል ተጠባባቂ ዳይሬክተር ጋሻው ገበየሁ፤ ኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ልማት መርሃ ግብርን ለመጀመር የወሰደችው ውሳኔ ደፋርና ሩቅ አሳቢነት ያመላከተ ነው ብለዋል። የሀገርን ዕድገት በአስተማማኝና ደኅንነቱ በተጠበቀ የኃይል አቅርቦት ልማትን ማሳለጥ እንደሚያስፈልግ የሚያስገነዝብ መሆኑንም ገልጸዋል። ለቀጣዩ ትውልድ ጠንካራና የበለጸገች ሀገር ማውረስ የሚያስችል ቁርጠኝነትን እንደሚያሳይም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ልማት መሻት በጤና፣ በትምህርት፣ በኢንዱስትሪ ዕድገትና በአካባቢ ጥበቃ ከማሳለጥ ባሻገር የኒውክሌር ባለሙያዎች፣ መሐንዲሶች፣ ተቆጣጣሪዎች፣ ተመራማሪዎችና የፖሊሲ አውጪ ትውልድ የሚቀርፅ ዕድል ነው ብለዋል። በቀጣይም በቴክኒክ ትብብር፣ በሰው ሃብት ልማት፣ ዓለም አቀፍ የማዕቀፍ ትግበራ እና ሌሎች መስኮች በትብብር ለመስራት ቁርጠኛ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
የምርምር ማዕከሉ የሩዝ ምርት እና ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰራ ነው
Dec 9, 2025 188
ጂንካ፤ህዳር 30/2018 (ኢዜአ)፡-የጂንካ ግብርና ምርምር ማዕከል የተሻሻሉ የሩዝ ዝርያዎችን በማላመድ የሩዝ ምርት እና ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን አስታወቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ምላሽና ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት የሩዝ ልማት ዕድገትን አስመልክተው ሲናገሩ በኢትዮጵያ ሩዝ በፎገራ አካባቢ ይመረት እንደነበረና ምርቱም ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል የዘለለ እንዳልሆነ ጠቁመዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ማብራሪያቸው በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ከ63 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ሩዝ እየተመረተ መሆኑን መግለፃቸውም የሚታወስ ነው። በአሁኑ ወቅት ከዚህ ቀደም ምንም ዓይነት ምርት በማይካሄድባቸው እንደ ሶማሌ ክልል ባሉ አካባቢዎች ሩዝ በስፋት እየለማ ይገኛል። መንግስት ለልማቱ ትኩረት በመስጠቱም በቅርብ ዓመታት ውስጥ ምርቱ ከተጠቀሰውም እንደሚልቅ ማሳያዎቹ በርካታ ናቸው። የጂንካ ግብርና ምርምር ማዕከልም የተሻሻሉ የሩዝ ዝርያዎችን በማላመድ የሩዝ ምርት እና ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል። የምርምር ማዕከሉ ቀደም ሲል በሩዝ ምርት በማይታወቁት በደቡብ ኦሞና በአሪ ዞኖች የተሻሻሉ አዳዲስ የሩዝ ዝርያዎችን በማላመድ ለአርሶና አርብቶ አደሩ እያስተዋወቀ ይገኛል። የምርምር ማዕከሉ ዳይሬክተር ተክሌ ዮሴፍ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለፁት አርሶ አደሩ ከተለመደ የአመራረት ዘይቤ ተላቆ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ግብርናውን እንዲያዘምን በሳይንሳዊ ጥናት የታገዘ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። አካባቢው ለሩዝ ምርት ተስማሚ መሆኑን የጠቆሙት ዳይሬክተሩ፥ በቀጣይም ሩዝ እንደ ሌሎች ሰብሎች በቋሚነት ማልማት እንዲቻል ማዕከሉ የዘር ብዜት ስራውን በስፋት እያከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በአካባቢው ያለውን ፀጋ እና ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ከውጭ የሚገባውን የሩዝ ምርት ለመተካት እየተሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል ። በምርምር ማዕከሉ የሰብል ተመራማሪ አወቀ ታደሰ በበኩላቸው ማዕከሉ በ10 ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ የሩዝ ዝርያዎችን ሲያላምድ መቆየቱን ጠቁመዋል ። ማዕከሉ ካላመዳቸው የሩዝ ዝርያዎች "ዕድገት'' ፣ ''ፎገራ-1" እና ''ፓዌ -2" የተሰኙ የሩዝ ዝርያዎች ለአካባቢው ስነ-ምህዳር ተስማሚና በሄክታር እስከ 78 ኩንታል ምርት መስጠት የሚችሉ በመሆናቸው ተመራጭ አድርጓቸዋል ብለዋል። በተለይ እነዚህ የሩዝ ዝርያዎች በአጭር ጊዜ ሊደርሱ የሚችሉ እና በበሽታና በተባይ የማይጠቁ በመሆናቸው ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል ። እስካሁን በደቡብ ኦሞ ዞን በግብርና ኢንቨስትመንት በተሰማሩ ባለሃብቶች በ230 ሄክታር መሬት ላይ በሙከራ ደረጃ የለሙ የሩዝ ዝርያዎች ውጤታማ መሆናቸውንም ጠቁመዋል። በዘርፉ የተሰማሩ የግል ባለሀብቶች የሩዝ ዝርያዎችን በስፋት ቢያለሙ በውጪ ምንዛሬ ከውጭ የሚገባውን የሩዝ ምርት በአገር ውስጥ ምርት መተካት እንደሚቻል ተናግረዋል፡፡ በደቡብ ኦሞ ዞን በናይ ጸማይ ወረዳ በግብርና ልማት ላይ የተሰማሩት አቶ ወርቁ ሮሮ፣ ከጂንካ ግብርና ምርምር ማዕከል ባገኙት የዘርና የክህሎት ድጋፍ በሙከራ ደረጃ በ3 ሄክታር መሬት ላይ ሩዝ ማልማታቸውን ጠቁመዋል። በዚህም 130 ኩንታል የሩዝ ምርት ማግኘታቸውን ጠቅሰው የሩዝ ምርት አዋጭና ጊዜና ጉልበት ቆጣቢ መሆኑን ጠቅሰው በ10 ሄክታር ላይ ለዘር ብዜት የሚሆን ሩዝ እያመረቱ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም የጀመሩትን የሩዝ ልማት ስራ የማስፋፋት ዕቅድ እንዳላቸውም አመልክተዋል።
በዲጂታል መታወቂያ ላይ ያለውን የማንነት መረጃ መጠበቅ የሚያስችል የዲጂታል ሰርተፍኬት አገልግሎት ይፋ ሆነ
Dec 9, 2025 153
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018(ኢዜአ)፦የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በዲጂታል መታወቂያ ላይ ያለውን የማንነት መረጃ መጠበቅ የሚያስችል የዲጂታል ሰርተፍኬት አገልግሎትን በይፋ አስጀምሯል። አገልግሎቱ በይፋዊ ቁልፍ መሰረተ ልማት ውስጥ የፋይዳ ደህንነት ማስጠበቂያ ቁልፎች የሚፈጠሩበትና የሚንቀሳቀሱበትን አሰራር ያካተተ ነው ተብሏል። እነዚህ ቁልፎች በዲጂታል መታወቂያ ላይ ያለውን የማንነት መረጃ ለመጠበቅ ጥቅም ላይ የሚውል የመተማመኛ ዲጂታል ፊርማ ለማዘጋጀት የሚውሉ መሆኑም ተገልጿል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ፤ ከዚህ ቀደም ለኤሌክትሮኒክ ፓስፖርት የዲጂታል ሰርተፊኬት አገልግሎት መጀመሩን ገልጸው፤ ዛሬ በይፋ የተጀመረው የፋይዳ መታወቂያ ሰርተፊኬት አገልግሎት ቀጣይ ስራ ነው ብለዋል። የሰርተፊኬት አገልግሎቱ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በከፍተኛ የደህንነት ደረጃዎች ባላቸው ቴክኖሎጂዎች የተጠበቀ እንዲሆን ያግዛል ነው ያሉት። የማንነት ስርቆትን ለመከላከል፣ማጭበርበር እና የማንነት መረጃን አላግባብ መጠቀምን ለመከላከል የሚያስችል መሆኑንም አመልክተዋል። ደህንነቱ የተጠበቀ ዲጂታል መታወቂያ ጤና፣ ትምህርት፣ ባንክን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶች በተሻለ መልኩ ለማግኘት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው መሆኑም ነው የተገለጹት። የፋይዳን ደህንነት ማረጋገጥ ደህንነቱ የተጠበቀ አገልግሎት ተደራሽ በማድረግ የተሳለጠ አገልግሎት እንዲኖር ዓይነተኛ ሚና እንደሚጫወት ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ ብሄራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና አስተባባሪ ዮዳሄ አርአያሥላሴ በበኩላቸው፤ 29 ሚሊዮን ዜጎች የፋይዳ መታወቂያ መመዝገባቸውን ተናግረዋል። መታወቂያ ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ ደህንነቱን ማስጠበቅ ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፤ ከዚህ አኳያ የሰርተፊኬት አገልግሎቱ መጀመር ትልቅ እርምጃ ነው ብለዋል። የሰርተፊኬት አገልግሎቱ የፋይዳ ዲጂታል ሰነዶች ተዓማኒነትን የሚጨምር መሆኑንም ጠቁመዋል።
የመደመር መንግስት ከዲጂታል ተደራሽነት ወደ ጋራ ብልፅግና የተጀመረውን ጉዞ ለማሳካት በትጋት ይሰራል- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Dec 9, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018 (ኢዜአ)፦ የመደመር መንግስት ከዲጂታል ተደራሽነት ወደ ጋራ ብልፅግና የተጀመረውን ጉዞ ለማሳካት፣ በመፍጠር፣ በመፍጠን እና በእመርታ መርሕ በትጋት እንደሚሰራ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ዲጂታል ኢኮኖሚን መገንባት ምርጫ ሳይሆን ብልጫ ነው! በሚል ርዕስ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ዛሬ ሁለተኛውን የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤን በይፋ ማስጀመራቸውን ገልጸዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን በውጤታማነት መተግበሩ፣ ለዜጎች ፈጣን፣ ቀልጣፋ እና ወጪ ቆጣቢ አገልግሎቶችን ተደራሽ ከማድረግ ባሻገር፣ የዕለት ከዕለት የኑሮ እንቅስቃሴን እያቀለለ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በተጨማሪም የኤሌክትሮኒክና የዲጂታል ግብይት ሥርዓትን ተመራጭ የክፍያ መንገድ እንዲሆን ማስቻሉን አመልክተዋል። ይሄም የሕዝብን ኑሮና የመንግሥትን አገልግሎት ከምርጫም በላይ ብልጫ ያለው እንዲሆን ያስችላል ነው ያሉት። ባለፉት አምስት ዓመታት በተዘረጋው የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት ውስጥ፣ በየዓመቱ ከ18.5 ትሪሊዮን ብር በላይ የገንዘብ ዝውውር እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ይሄንን ስኬት በላቀ መልኩ በማስቀጠል ሁሉን አቀፍ ብልፅግናን የማሳካት ግብ የያዘውን የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን በቅርቡ በሚኒስትሮች ምክር ቤት መጽደቁን አውስተዋል። ስትራቴጂው ዲጂታል መሠረተ ልማትን የማጠናከር፣ ተደራሽነትን ብቻ ሳይሆን አጠቃቀምን ለማስፋት ክሂሎትን የመገንባት እና ችግር ፈቺ ፈጠራን የማበረታታት ዓላማ ያለው መሆኑን ጠቅሰው ለስኬታማነቱ ሁሉም ሚናውን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የመደመር መንግሥት ከዲጂታል ተደራሽነት ወደ ጋራ ብልፅግና የጀመርነውን ጉዞ ለማሳካት፣ በመፍጠር፣ በመፍጠን እና በእመርታ መርሕ ይተጋል ሲሉም ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የዲጂታል ፋይናንስና የክፍያ ሥርዓት በፈጣን የዕድገት ጎዳና ላይ ነው- የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ(ዶ/ር)
Dec 9, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30፣ 2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የዲጂታል ፋይናንስና የክፍያ ሥርዓት በፈጣን የዕድገት ጎዳና ላይ መሆኑን የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ። ከ2026 - 2030 የሚተገበረው ብሔራዊ የዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ ዛሬ በሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህና ሌሎችም የመንግሥት ከፍተኛ አመራር አባላት በተገኙበት ይፋ ተደርጓል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ( ዶ/ር) በኢትዮጵያ የዲጂታል ለውጥ ከፍተኛ እድገት ላይ እንደሚገኝ በአፅንኦት ገልጸዋል። የዲጂታል ክፍያ ሥርዓቶች ከፍተኛ ተቀባይነት እያገኙ እና ለኢኮኖሚ እድገት ጉልህ ሚና እያበረከቱ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ አስደናቂ የሆነ የዲጂታል ለውጥ እያስተናገደች መሆኗን ገልጸው፤ ይህም ለፋይናንስ ዘርፉ ዕድገት ትልቅ መስፈንጠሪያ እየሆነ መምጣቱን አንስተዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ፈጠራን የሚያበረታቱ አሠራሮችና በዲጂታል መሠረተ ልማት ላይ እየተደረጉ ያሉ ኢንቨስትመንቶችም ለዕድገቱ ሚናቸው የላቀ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ የዲጂታል ግብይቶች ፈጣን ዕድገት እያሳዩ ነው ያሉት የባንኩ ገዥ፤ ይህም በሀገሪቷ የግብይት ገጽታ ላይ ታሪካዊ ለውጥ ማምጣቱን ጠቁመዋል። ይህ የዲጂታል ግብይት መጨመር፣ የዲጂታል ክፍያዎች ተቀባይነት እየጨመረ መምጣቱን የሚያሳይ መሆኑንም ተናግረዋል። በብሔራዊ የክፍያ መሠረተ ልማቶች ላይ እየተደረጉ ያሉ የማሻሻያ ሥራዎች ቅልጥፍናንና ደህንነትን እያሻሻሉ ሲሆን፤ ጠንካራ የዲጂታል ፋይናንስ ሥርዓት እንዲኖር መሠረት እየጣሉ ነው ብለዋል። ሰፊ የዲጂታል እምቅ አቅም ያላት ኢትዮጵያ በፍጥነት እያደገ ያለ የፋይናንስና የግብይት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን ገልጸዋል። እነዚህ ስኬቶች ቢኖሩም በቴክኖሎጂ ተደራሽነት ያሉ ክፍተቶች፣ የአጣዳፊ ጊዜ አገልግሎቶች አለመስፋት እና እያደጉ የመጡ የሳይበር ደህንነት ስጋቶችን ጨምሮ ፈተናዎች መኖራቸውን ጠቅሰዋል። እነዚህን ፈተናዎች ለመፍታት በመንግሥት እና የግል ዘርፉ ትብብር አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። የብሔራዊ ዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ (2026-2030) በፋይናንስ አገልግሎት ውስጥ አካታችነትን እንደሚያጎለብት እና ፈጠራን እንደሚያበረታታም ነው የገለጹት ገዥው። አዲሱ ስትራቴጂ አስተማማኝ እና ተዓማኒ የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት መዘርጋት፣ የፋይናንስ አገልግሎቶች ዲዛይን ውስጥ የፆታ አቀፍ ተጠቃሚነትን ማሳደግ እና ከድንበር ተሻጋሪ ክፍያዎች ጋር የሚጣጣም የክፍያ ስርዓትን መፍጠርን ያካትታል ብለዋል። በተጨማሪም ስትራቴጂው የብሔራዊ መረጃ ልውውጥ እንዲቋቋም እና የአስፈላጊ አገልግሎቶችን ተደራሽነት ለማስፋት ድጋፍ እንደሚያደርግ አስረድተዋል።
ኢትዮጵያ የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ጠንካራ ዲጂታል ኢኮኖሚ እየገነባች ነው- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Dec 9, 2025 99
አዲስ አበባ፤ ህዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ጠንካራ ዲጂታል ኢኮኖሚ እየገነባች መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ፤ ከ2026 - 2030 የሚተገበረውን ብሔራዊ የዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ ይፋ አድርገዋል። ሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጉባኤው መክፈቻ ባደረጉት ንግግር፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን በተሳካ ሁኔታ በመተግበር ዘርፈ ብዙ ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ተጨባጭ የዲጂታል እድገት ማስመዝገቧን ጠቅሰው፤ የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎት ተደራሽነት በሚያስደንቅ ፍጥነት መስፋፋቱን ተናግረዋል። መንግሥት በወሰዳቸው የሪፎርም እርምጃዎች እና የመሠረተ ልማት ግንባታ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ጠንካራ መሠረት መገንባቱን ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅት የዲጂታል ፋይናንስ ምህዳሩ በየዓመቱ ከ18 ነጥብ 5 ትሪሊዮን ብር በላይ ግብይቶችን እያስተናገደ ነው ብለዋል። የዘርፉ ለውጥ ፈጣንና አስተማማኝ የቴሌኮምና የኢንተርኔት ተደራሽነትን በማስፋት የኢኮኖሚውን ዲጂታል ጉዞ እያፋጠነ መሆኑን ገልጸዋል። የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ) እና መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ያሉ የዲጂታል የመንግሥት አሠራሮች በመቶዎች የሚቆጠሩ አገልግሎቶችን በአንድ ስፍራ በማሳለጥ እንግልትን እየቀነሱና ግልጽነትን እያሻሻሉ መሆኑን ተናግረዋል። ብሔራዊ ባንክ አሠራሮችን በማዘመን ለሞባይል ገንዘብ ዝውውር፣ ለክፍያ አገልግሎት ሰጪዎች እና ለፈጠራ ባለሙያዎች ምቹ ምህዳር መፍጠሩን ተናግረዋል። በኢት-ስዊች የተደገፈው ብሔራዊ የዲጂታል ክፍያ አሠራር ከፍተኛ ገንዘብ በባንኮች መካከል እና በዲጂታል አማራጭ በቀላሉ እንዲንቀሳቀስ አስችሏል ነው ያሉት። የቴሌብር ፈጣን ተደራሽነትና ለአጠቃቀም ምቹ መሆኑ የዕለት ተዕለት የዜጎችን ኑሮ እያሳለጠ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭን ጨምሮ ዲጂታል ክህሎትን የማጎልበት ሥራዎች ትኩረት እንደተሰጣቸው ተናግረዋል። በዲጂታል ዘርፉ የተመዘገቡ ስኬቶች ኢኮኖሚውን ወደ ፊት የሚያሻግሩ ብሔራዊ መሠረተ ልማቶች መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ነገር ግን ከተደራሽነት ባሻገር ትርጉም ባለው አጠቃቀም ላይ ትኩረት ማድረግ ይገባል ነው ያሉት። የዲጂታል አጠቃቀምን ማሳደግ የአርሶና አርብቶ አደሮችን ህይወት በማሻሻል፣ ሥራቸውን በማቅለል፣ የፋይናንስ አገልግሎትን በቀላሉ እንዲያገኙ በማድረግ የአካታች ኢኮኖሚ ዕድገት ይፋጠናል ብለዋል። የዲጂታል ጉዟችን ቀጣዩ ምዕራፍ ሊለካ የሚገባው የህዝባችንን ህይወት በማሻሻል ረገድ ነው ሲሉም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል። ከዚህ አኳያ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መሠረተ ልማትን እንድናጠናክር፣ አጠቃቀምን ማስፋት፣ ክህሎቶችን መገንባት እና ችግሮችን የሚፈታ ፈጠራን የማበረታታት ዓላማ ያነገበ መሆኑን ገልጸዋል። ዘመኑን የዋጀው ይህ ስትራቴጂ፣ በሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ፣ አስተዳደራዊ እና ማህበራዊ ዘርፎች ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን ዋነኛ አንቀሳቃሽ ኃይል የሚያደርግ መሆኑን ጠቅሰዋል። የዲጂታል ግብይት ማህበረሰቡን የሳይበር ደህንነትን በማረጋገጥ ግልጽነት፣ ተጠያቂነት እና ኃላፊነት በተሞላበት አሠራር ህዝቡን ማገልገል እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል። ሁሉንም ባለድርሻ አካላት በጋራ ዓላማ በማሳተፍ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን የሚሆን ዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የዲጂታል መፃኢ ዕድሏን የሚወስን ጠንካራ መሠረት አስቀድማ ገንብታለች ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በቀጣይ ከዲጂታል ተደራሽነት ወደ ተፅዕኖ እና ወደ ጋራ ብልጽግና የሚደረገውን ሽግግር ማፋጠን እንደሚገባ ጠቁመዋል።