ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
የብዙኃን ትራንስፖርት ፍላጎትን ከማሟላት አኳያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው
Dec 4, 2025 34
አዲስ አበባ፤ ህዳር 25/2018(ኢዜአ)፦ የብዙኃን ትራንስፖርት ፍላጎትን ከማሟላት አኳያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በረኦ ሃሰን ገለጹ። መንግስት በኤሌክትሪክ ኃይል የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ለማስፋት ልዩ ትኩረት ሰጥቷል። ሚኒስትር ዴኤታው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት መጠነኛ መቀመጫ ባላቸው ወንበሮች የትራንስፖርት ፍላጎት ማሟላት አዳጋች መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም መንግስት አማራጭ የተሽከርካሪ አቅርቦትን በማስፋት የትራንስፖርት አገልግሎት ተደራሽነት ለማረጋገጥ እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በኤሌክትሪክ ኃይል የሚሰሩ ተሽከርካሪዎች ያላቸው ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ የጎላ መሆኑን ጠቁመው፤ መንግስት በስፋት ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገቡና አገልግሎት እንዲሰጡ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝም አመልክተዋል። በተለይም በፖሊሲው የተካተተውን የብዙሃን ትራንስፖርት ፍላጎት ከማሟላት አኳያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዚህም የትራንስፖርት አገልግሎቱን በእጅጉ በማሳለጥ በየጊዜው እየጨመረ ላለው የብዙሃን ትራንስፖርት ፍላጎት ምላሽ እየሰጠ ስለመሆኑ ገልጸዋል። በቅርቡ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተግባራዊ የተደረጉ 110 የብዙሃን ትራንስፖርት ማመላለሻ ''ቬሎሲቲዎች'' እጥረት ባሉባቸው 11 መስመሮች እንዲሰማሩ የተደረገ ሲሆን፤ በዚህም ከፍተኛ ለውጥ መጥቷል ብለዋል። እንዲሁም 22 በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ሚኒባሶች ከቬሎሲቲዎቹ ጋር ተጣጥመው አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉን ጠቅሰው፤ ይህም የትራንስፖርት ፍላጎትን ተደራሽ ለማድረግ ዓይነተኛ ሚና አለው ነው ያሉት። እንዲሁም በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የታክሲ አገልግሎት የሚሰጡ አደረጃጀቶች እየተፈጠሩ መሆኑ ጠቁመው፤ ለዚህም ከግሉ ዘርፍ ጋር በመተባበር የትራንስፖርት አገልግሎቱን ተደራሽ የማድረግ ሂደት እንዳለ አብራርተዋል። ኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ተግባራዊ ማድረግ ከጀመረችበት ጊዜ አኳያ አሁን የደረሰችበት ደረጃ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ከፍ ያደርገዋልም ብለዋል። በተለይም የግለሰብ ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ የብዙሃን ትራንስፖርትን ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ማስገባት መጀመሩ ትልቅ እምርታ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል። ይህም ዘርፉ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት ያለው ፋይዳ እንዲጨምር በማድረግ በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ አበርክቷል ነው ያሉት።
በዲጂታል ዘመን የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመከላከልና መፍትሄ ለመስጠት አዲስና ዓለም አቀፋዊ የትብብር ሞዴል መገንባት ያስፈልጋል
Dec 3, 2025 128
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 24/2018(ኢዜአ)፦ በዲጂታል ዘመን የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመከላከልና መፍትሄ ለመስጠት አዲስና ዓለም አቀፋዊ የትብብር ሞዴል መገንባት እንደሚያስፈልግ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ። የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ያዘጋጀው የ2025 ዳይመንድ ክለብ ሲምፖዚየም "አካታች ወደፊትን ለመፍጠር ዓለም አቀፍ የዲጂታል አመራር ማጠናከር" በሚል መሪ ሃሳብ ተካሄዷል። በሲምፖዚየሙ መክፈቻ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ ዲጂታል እድገት አበረታች መሆኑን ገልጸው፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች በዲጂታል መለያ ሥርዓቶች ውስጥ እየተካተቱ መሆኑን አስታውቀዋል። የዲጂታል መሠረተ ልማቶች እየተስፋፉ እንዲሁም በኤሌክትሮኒክ የሚሰጡ የመንግስት አገልግሎቶች እያደጉ መምጣታቸውን በአብነት አንስተዋል። በቅርቡ የፀደቀው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካታች የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥና የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማጎልበት ቁልፍ ሚና እንዳለው አጽንኦት ሰጥተዋል። በዓለም ላይ ቴክኖሎጂን በአግባቡ አለመጠቀም አዲስ ፈተና የመፍጠር አቅም እንዳለው ጠቁመው፤ ይህን ፈተና ለመሻገር ሀገራት ትብብራቸውን ማጠናከር አለባቸው ብለዋል። የመረጃ ግላዊነት፣ የሳይበር ደህንነት እና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ላይ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች በአንድ ሀገር አቅም ሊፈቱ እንደማይችሉ አመላክተዋል። በመሆኑም በዲጂታል ዘመን የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመከላከልና መፍትሄ ለመስጠት አዲስና ዓለም አቀፋዊ የትብብር ሞዴል መገንባት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል። የአዲስ አበባ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ደረጄ እንግዳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዘመኑ ዲጂታል ቴክኖሎጂ ዓለምን ባልተጠበቀ ፍጥነት እየቀረጸ ያለበት ጊዜ መሆኑን ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው ባሉት የልህቀት ማዕከላት በመታገዝ በአህጉር ደረጃ ተጽዕኖ ፈጣሪ ለመሆን እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ተቋሙ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ላይ ያተኮረ ፈር ቀዳጅ ዩኒቨርሲቲ መሆኑን አስታውሰው፤ የአፍሪካን ቴክኖሎጂ የሚቀርጹ ተመራማሪዎች እና ዲጂታል መሪዎች ለማፍራት ቁርጠኛ መሆኑን ጠቁመዋል። የዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂ ፕሮፌሽናል ፕሮግራም ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ጁንሴኦክ ሀዋንግ መድረኩን ላዘጋጁ አካላት ምስጋና አቅርበዋል። ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጋር የተለያዩ ስራዎችን በጋራ እያከናወኑ መሆኑን ገልጸው፤ ትብብሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በቀጣይም ትልቁን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ ለመክፈት አመራሩ ቁርጠኛ መሆኑን አመላክተዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካታች የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ ቁልፍ ሚና ይጫወታል
Dec 3, 2025 150
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 24/2018 (ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካታች የኢኮኖሚ ዕድገትን ይበልጥ ለማረጋገጥ ቁልፍ ሚና የሚጫወት መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ። የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ያዘጋጀው የ2025 'ዳይመንድ ክለብ ሲምፖዚየም' Club Symposium) "አካታች ወደ ፊትን ለመፍጠር ዓለም አቀፍ የዲጂታል አመራር ማጠናከር" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው። በሲምፖዚየሙ መክፈቻ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ባደረጉት ንግግር ቴክኖሎጂ የዓለምን ከባድና ወስብስብ ችግሮች ለመፍታት ዕድሎችን ይዞ መምጣቱን ተናግረዋል። በሌላ በኩል ቴክኖሎጂን በአግባቡ አለመጠቀም አዲስ ፈተናዎችን የመፍጠር አቅም እንዳለው ጠቁመው፤ ይህን ፈተና ለመፍታት ሀገራት ትብብራቸውን የበለጠ ማጠናከር አለባቸው ብለዋል። በቅርቡ የፀደቀው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካታች የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥና የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማጎልበት ቁልፍ ሚና እንዳለውም ነው አጽንኦት የሰጡት። የኢትዮጵያ ዲጂታል እድገት አበረታች መሆኑን ገልጸው፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች በዲጂታል መለያ ሥርዓቶች ውስጥ እየተካተቱ መሆኑን ተናግረዋል። የዲጂታል መሠረተ ልማቶች እየተስፋፉ እንዲሁም ኤሌክትሮኒክ የመንግስት አገልግሎቶች እያደጉ መምጣታቸውን አንስተዋል። የመረጃ ግላዊነት፣ ሳይበር ደህንነት እና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ላይ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች በአንድ ሀገር ብቻ ሊፈቱ እንደማይችሉ አመላክተዋል። የሰዎች መብቶች የሚጠበቅበት እና ፈጠራን ከድንበር በላይ እንዲያድግ የሚያስችል አዲስ ዓለም አቀፍ የትብብር ሞዴሎች መገንባት እንደሚገባም ጠቁመዋል። የዛሬው ሲምፖዚየም ለመነጋገር ብቻ ሳይሆን ወደ ተግባር ለመሸጋገር የሚያስችል ጊዜ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል።
በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ዕውቀት ቀስመናል- የአሪ ዞን ሰልጣኞች
Dec 3, 2025 90
ጂንካ፤ ህዳር 24/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ዕውቀት መቅሰማቸውን የአሪ ዞን የኢትዮ ኮደርስ ሰልጣኞች ተናገሩ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሺዬቲቭ በሀገሪቱ በዲጂታል ክህሎት የታገዘ ማህበረሰብን ለመፍጠርና ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት የሚያግዝ የኢትዮ -ኮደርስ ስልጠና በሁሉም አካባቢዎች እየተሰጠ ነው። በስልጠናው ላይ እየተሳተፉ የሚገኙ የአሪ ዞን ወጣቶችም ስልጠናው የዲጂታል ክህሎታቸውን በማሳደግ በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርጋቸውን እውቀት አንደቀሰሙ ተናግረዋል። በዞኑ የጂንካ ከተማ ነዋሪ ገላዬ ስምዖን፥ መንግስት በነፃ ለዜጎች ያመቻቸው የ5 ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ክህሎታቸውን በማሳደግ በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርጋቸውን እውቀት ማግኘታቸውን ጠቁመዋል ። በአሁኑ ወቅት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ዕውቀትን ማሳደግ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል አቅም ለመፍጠር እንደሚያግዝ ጠቅሶ፥ ስልጠናው ዲጂታል ኢትዮጵያን በመገንባት ሀገራዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ ለተጀመረው ጥረት አጋዥ መሆኑንም ገልጸዋል። በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እና በዳታ አናሊስስ ኮርሶችን ያጠናቀቀው ገላዬ ስምኦን፥ በተለይ የዳታ አናሊስስ ኮርስ ለሁለተኛ ዲግሪ ማሟያ ለሚሰራው የመመረቂያ ፅሁፍ በእጅጉ እንዳገዛቸው አስረድተዋል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ የጂንካ ከተማ ነዋሪው ወጣት ኬብሮም ዕቁባይ በበኩሉ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለወጣቱ ትልቅ እድል ይዞ መምጣቱን ተናግሯል። ስልጠናው ጠቃሚና አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ዕውቀት እንደሚያስጨብጥ ገልፆ በዳታ ሳይንስ እና በፕሮግራሚንግ የሚሰጠውን ስልጠና በማጠናቀቅ ሰርተፊኬት ማግኘቱን ጠቁሟል ። በአሪ ዞን መንግስት ኮሙኒኬሽን መምሪያ የማህበራዊ ሚዲያ ሪፖርተር እየሩሳሌም ይንቲሶ በበኩሏ ስልጠናው ለጋዜጠኝነት ሙያ እጅግ አጋዥና የዲጂታል ዕውቀትን የሚያልቅ እንደሆነም ጠቁማለች። በፕሮግራሙ ከሚሰጡ አራት ስልጠናዎች አርቲፊሻል ኢንተለጀንስና ዳታ አናሊስ ኮርሶችን ማጠናቀቋን ጠቁማ፥ በዌብ-ፕሮግራሚንግ እና የአንድሮይድ ማበልፀግ ኮርሶችን ለማጠናቀቅም ማቀዷን ገልፃለች። ሌሎች ወጣቶችም የዚህ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማህበራዊ ሚዲያ ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ እየሰራች እንዳለችም ተናግራለች። የአሪ ዞን ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ይኼነው ተስፋዬ በበኩላቸው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን ውጤታማ ለማድረግ ከሌሎች ተቋማት ጋር በመቀናጀት በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ገለጸዋል። በዞኑ በሶስት ዓመታት ውስጥ ከ12 ሺህ 400 በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች ስልጠናውን ለመስጠት መታቀዱን ጠቁመው ካለፈው ዓመት እስካሁን ከ4 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች ስልጠናው መሰጠቱን ጠቁመዋል። ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ቢሮ በተገኘ መረጃ መሰረት በክልሉ ከ235 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለመስጠት እየተሰራ መሆኑም ተመላክቷል።
ተቋማት እና ዘርፎች የሰው ሰራሽ አስተውሎት አጠቃቀምን የውጤት መለኪያቸው ማድረግ አለባቸው
Dec 2, 2025 178
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 23/2018(ኢዜአ)፦ እያንዳንዱ ተቋም እና ዘርፍ የሰው ሰራሽ አስተውሎትን አጠቃቀምን የውጤት እና ግብ መለኪያ በማድረግ ሊሰራ እንደሚገባው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አስገነዘቡ። “በመደመር መንግሥት ዕይታ፣ የዘርፎች እመርታ” ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች የማጠቃለያ ስልጠና በሰጡበት ወቅት ካነሷቸው ሀሳቦች መካከል አንዱ የዲጂታል ዘርፉን የተመለከተ ይገኝበታል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዲጂታል ዘርፉን አስተሳሰሪ አቅም መሆኑን ገልጸው መንግስት የዲጂታል መታወቂያ፣ ሞባይል ባንኪንግ እና ዘመናዊ የክፍያ ዘዴዎች የማስፋት ስራ እያከናወነ መሆኑን አመልክተዋል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት እና ኳንተም ሳይንስ የሰው ልጆች አኗኗር፣ ስራ እና እሳቤ እየየቀሩ እንደሚገኙም ገልጸዋል። ቴክኖሎጂን መቀበል አለብን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሰው ሰራሽ አስተውሎት የኃይልን፣ የምርት እና የተሳትፎ ሕግጋትን እንደገና እየጻፈ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ፋይዳ፣ ፓስፖርት፣ መሶብ፣ ሞባይል ባንኪንግ፣ ዘመናዊ የክፍያ ዘዴ፣ የጉምሩክ እና ገቢዎች ዲጂታል አገልግሎት እንዲሁም የተቀናጀ የፋይናንስ አስተዳደር መረጃ ሥርዓት(ኢፍሚስ) በሀገር ውስጥ አቅም እየጎለበተ እና እያደገ መሄድ እንዳለበትም አስገንዝበዋል። የተለያዩ ዘርፎች ምን ያህል ሰው ሰራሽ አስተውሎትን ተጠቅመዋል? ብለን ከአሁኑ መለካት ካልጀመርን ዘመን መዋጀትን ብንፈልግም አንደርስበትም ነው ያሉት። ለሁሉም ስራ ቴክኖሎጂን መጠቀም እንደሚያስፈልግ ጠቁመው የተሟላ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የተለያዩ ቴክኖሎጂዎች ጋር ማስተሳሰር ግድ እንደሚል አስገንዝበዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአንድ ግቦች በሚል ባነሱት ሀሳብ እያንዳንዱ ከተማ የአንድ መሶብ አገልግሎት መክፈት እንዳለበትም አንስተዋል። በ100 ፐርሰንት ግቦች ውስጥም የፋይዳ መታወቂያ ሙሉ ለመሉ በኢትዮጵያ መዳረስ እንዳለበት ገልጸው ለዚህም በሁሉም የአስተዳደር መዋቅሮች አበክሮ መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ በጣም ወሳኝ ስራ መሆኑን ጠቁመውም ኢኒሼቲቩ መቶ ፐርሰን መሳካት አለበት ብለዋል። እያንዳንዱ ተቋም እና ዘርፍ የሰው ሰራሽ አስተውሎትን ምን ያህል ተጠቀምኩኝ? በሚል ግብ ማስቀመጥ እንደሚኖርበትም ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት። የሰው ሰራሽ አስተውሎት አጠቃቀም ካላደገ የሚታሰበውን ትራንስፎርሜሽንና ትስስር ማምጣት እንደማይቻልም አመልክተዋል። በፈጠራ እና ፍጥነት ጥራትንና ብዛትን እውን ለማድረግ መትጋት የመደመር መንግስት ቁልፍ ስራ ነው ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ተናግረዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት መሰረት የሆኑ ቁልፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ አስችሏል
Dec 1, 2025 252
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት መሰረት የሆኑ ቁልፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ ማስቻሉን የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉቀን ቀሬ ገለጹ። የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች የተተከሉ ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎችን በይፋ አገልግሎት አስጀምሯል። የContinious Operating Reference Station /CORS/ -ጣቢያ በቋሚነት መሬት ላይ የሚተከል የሳተላይት መረጃን ያለማቋረጥ የሚቀበልና የሚያደራጅ ቴክኖሎጂ ነው ተብሏል። እንዲሁም የአንድን ቦታ መገኛ ከጂ ፒ ኤስ ሳተላይቶች 24 ሰዓት በመቀበል ከፍተኛ ጥራት ያለው መረጃ የሚያቀርብ እንደሆነም ተገልጿል። የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉቀን ቀሬ እንደገለጹት፥ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ባለፉት አምስት ዓመታት ለዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት መሰረት የሆኑ ቁልፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ አስችሏል። የዲጂታል መታወቂያ ምዝገባን በማስጀመረ፣ በቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ግንባታ፣ በህግ ማእቀፎች እንዲሁም በ5 ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ በክህሎት ግንባታ ለውጥ መምጣቱን ጠቁመዋል። ከሳተላይት መረጃ መቀበያ ጀምሮ የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ግንባታ ላይ ሠፋፊ ተግባራት መከናወናቸውን በማንሳት፥ በቀጣይም ለዲጅታል መሠረተ ልማትና ለዲጅታል ኢኮኖሚ መስፋፋት በትብብር እንደሚሠራ ጠቁመዋል። የከተማ እና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን በበኩላቸው፥ ዛሬ ሥራ የጀመሩት ጣቢያዎች በከተሞች እየተመዘገበ ያለውን እመርታዊ ለውጥ በማጠናከር ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አንስተዋል። በተለይም ከተሞችን በፕላን እንዲሁም በከተሞች ያለ መሬትን ቆጥሮ መዝግቦ በፍትሀዊነት ለመምራት እና የቅየሳን ትክክለኛነትን ለማረጋገጥ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖራቸው ጠቅሰዋል። ከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር በቀጣይም 14 ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎች (Continious Operating Reference Station /CORS/ ለመገንባት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ (ዶ/ር)፥ ዛሬ ሥራ የጀመሩት መረጃ ተቀባይ ጣቢያዎች ለቅየሳ ሙያተኞች፣ ለተመራማሪዎች፣ ለአደጋ ስጋት ተንታኞች፣ ለመልክዓ ምድር እና ለልዩ አገልግሎት ካርታ አዘጋጅ ባለሙያዎች የቦታዎችን አሁናዊ ሁኔታ መረጃ ለማግኘት እንደሚያስችሉ ገልጸዋል። የህንጻ፣ የመንገድ፣ የድልድይ እና ግድብ ግንባታ ፕሮጀክቶች ጥራት ባለው ጂኦስፓሻል መረጃ ላይ ተመስርተው እንዲነደፉና እንዲገነቡ ከፍተኛ ፋይዳ እንዳላቸው ጠቁመዋል። የግብርና፣ የኢንዱስትሪ፣ የማዕድንና ሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች እንዲዘምኑ በቂ መረጃ በማቅረብ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖራቸውም ነው ያነሱት። በተጨማሪም የመሬት አስተዳደር ዘመናዊ እና ጥራት ያለው እንዲሆን ያስችላሉ ብለዋል። ኢንስቲትዩቱ ጣቢያዎቹን ለቅየሳ ስራዎች እና ለካርታ ዝግጅት እንዲሁም ምርምር ለመስራት በሰፊው እንደሚጠቀምባቸው አንስተዋል።
የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎችን አገልግሎት አስጀመረ
Dec 1, 2025 242
አዲስ አበባ፤ ህዳር 22/2018(ኢዜአ)፦የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች የተተከሉ ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎችን በይፋ አገልግሎት አስጀምሯል። የከተማ እና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን በዚሁ ወቅት፥ ዛሬ ሥራ የጀመሩት ጣቢያዎች በከተሞች እየተመዘገበ ያለውን እመርታዊ ለውጥ በማጠናከር ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አንስተዋል። በተለይም ከተሞችን በፕላን እንዲሁም በከተሞች ያለ መሬትን ቆጥሮ መዝግቦ በፍትሀዊነት ለመምራት እና የቅየሳን ትክክለኛነትን ለማረጋገጥ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖራቸው ጠቁመዋል። በመረጃ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ አሰጣጥን በማዳበር እና ተጠቃሚዎች በቀላሉ ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላሉ ነው ያሉት። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር በቀጣይም 14 ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎች (Continious Operating Reference Station /CORS/ ለመገንባት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉቀን ቀሬ በበኩላቸው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለዲጂታል ልማት መሰረት የሆኑ ቁልፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ ማስቻሉን ጠቁመዋል። የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ግንባታ ላይ ሠፋፊ ተግባራት መከናወናቸውን በማንሳት፥ በቀጣይም ሚኒስቴሩ ከሳተላይት መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎችን ለማስፋፋት በትብብር እንደሚሠራ ጠቁመዋል። የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ (ዶ/ር)፥ ዛሬ ሥራ የጀመሩት መረጃ ተቀባይ ጣቢያዎች ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተሟላላቸው ናቸው ብለዋል። ለቅየሳ ሙያተኞች፣ ለተመራማሪዎች፣ ለአደጋ ስጋት ተንታኞች፣ ለመልክዓ ምድር እና ለልዩ አገልግሎት ካርታ አዘጋጅ ባለሙያዎች የቦታዎችን አሁናዊ ሁኔታ መረጃ ለማግኘት እንደሚያስችሉ ገልጸዋል። የህንጻ፣ የመንገድ፣ የድልድይ እና ግድብ ግንባታ ፕሮጀክቶች ጥራት ባለው ጂኦስፓሻል መረጃ ላይ ተመስርተው እንዲነደፉና እንዲገነቡ ከፍተኛ ፋይዳ እንዳላቸው ጠቁመዋል። የግብርና፣ የኢንዱስትሪ፣ የማዕድንና ሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች እንዲዘምኑ በቂ መረጃ በማቅረብ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖራቸውም ነው ያነሱት። በተጨማሪም የመሬት አስተዳደርን ዘመናዊ እና ጥራት ያለው እንዲሆን ያስችላሉ ብለዋል። ኢንስቲቲዩቱ ይህን ጣቢያዎቹን ለቅየሳ ስራዎች እና ለካርታ ዝግጅት እንዲሁም ምርምር ለመስራት በሰፊው እንደሚጠቀምባቸው አንስተዋል። የContinious Operating Reference Station /CORS/ -ጣቢያ በቋሚነት መሬት ላይ የሚተከል የሳተላይት መረጃን ያለማቋረጥ የሚቀበልና የሚያደራጅ ቴክኖሎጂ ነው ተብሏል። እንዲሁም የአንድን ቦታ መገኛ ከጂ ፒ ኤስ ሳተላይቶች 24 ሰዓት በመቀበል ከፍተኛ ጥራት ያለው መረጃ የሚያቀርብ እንደሆነም ተገልጿል።
የአፍሪካ ህብረት ያዘጋጀው የመጀመሪያው የዲጂታል ግብርና ኮንፍረንስ ዛሬ በአዲስ አበባ ይጀመራል
Dec 1, 2025 195
አዲስ አበባ፤ ህዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት ያዘጋጀው የመጀመሪያው የዲጂታል ግብርና ኮንፍረንስ በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል። “ኢኖቬሽን እና የዲጂታል መፍትሄዎችን ጠንካራ፣ አረንጓዴ እና በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብርና ዘርፍ ግንባታ በመጠቀም የአፍሪካን መጻኢ ጊዜ ብሩህ ማድረግ” የኮንፍረንሱ መሪ ሀሳብ ነው። የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ፣ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴሽን አገልግሎት፣ የግብርና ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን፣ የገበያ ተደራሽነት፣ የእሴት ሰንሰለትን ማጠናከር፣ የግብርና ምርታማነትን ከአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም መገንባት ጋር ያስተሳሰረ አካሄድን መከተል፣ የግብርና ፖሊሲዎችና የህግ ማዕቀፎች ትግበራ በኮንፍረንሱ የሚመከሩባቸው አጀንዳዎች ናቸው። ኮንፍረንሱ የእውቀት ሽግግር እና ፖሊሲ ተኮር ውይይቶች የሚደረግበት ሲሆን ስኬታማ የሀገራት የግብርና ኢኒሼቲቮች ለተሳታፊዎች ይቀርቡበታል። በአፍሪካ የዲጂታል ግብርና መፍትሄዎችን ተደራሽነት የሚደግፉ ስትራቴጂዎች የመለየት እና አጋርነቶችን ማጠናከር ከሁነቱ የሚጠበቅ አበይት ውጤት መሆኑን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። ኮንፍረንሱ የአፍሪካ ህብረት እ.አ.አ 2024 ያፀደቀውን አህጉራዊ የዲጂታል ግብርና ስትራቴጂ ተፈጻሚነት የማሳደግ ጥረት አካል መሆኑንም አመልክቷል። የግብርና ስትራቴጂው ከአጀንዳ 2063 እና ከረጅም ጊዜ የአፍሪካ የልማት እቅድ ጋር የተጣጣመ መሆኑን ነው ህብረቱ የገለጸው። ስትራቴጂው ኢንፎርሜሽንና ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ(አይሲቲ) በመጠቀም አህጉራዊ የዲጂታል ገበያ መገንባት እና ግብርናን ከአፍሪካ የዲጂታልና ዘላቂ ልማት ግቦች ጋር የማስተሳሰር ግብ ያለው ነው። እስከ ሕዳር 24 ቀን 2018 ዓ.ም በሚቆየው በዚህ መድረክ የአፍሪካ ሀገራት ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እና ፖሊሲ አውጪዎች፣ የግብርና ተመራማሪዎች እና ሳይንቲስቶች፣ የቴክኖሎጂ ባለሙያዎች፣ አርሶ አደሮች እና የአርሶ አደር ተቋማት፣ የምርምር ተቋማት፣ባለሀብቶች፣ የልማት አጋሮች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ይሳተፋሉ።
የኢዜአ ጋዜጠኛ ጌትነት ሸንቁጤ በዲጂታል ሚዲያ ዘርፍ የሶስተኛው የኢጋድ የሚዲያ ሽልማትን አሸነፈ
Nov 30, 2025 248
አዲስ አበባ፤ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ጋዜጠኛ ጌትነት ሸንቁጤ በዲጂታል ሚዲያ ዘርፍ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የ2025 የሚዲያ ሽልማት አሸናፊ ሆኗል። ሽልማቱን የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ዋና ፀሀፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) እጅ ተረክቧል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የ2025 የሚዲያ ሽልማት በአዲስ አበባ ስካይ ላይት ሆቴል በመካሄድ ላይ ነው። የሽልማት ስነ ስርዓቱ “ውጤታማ የአየር ንብረት ዘገባ ደህንነቱ ለተረጋገጠ፣ ጠንካራ እና የተረጋጋ ቀጣና” በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)፣ የኢጋድ ዋና ፀሀፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)፣ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በመድረኩም የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋዜጠኛ ጌትነት ሽንቁጤ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የ2025 የሚዲያ ሽልማት በዲጂታል ሚዲያ ዘርፍ አሸናፊ በመሆን ሽልማቱን ተቀብሏል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት በዲጂታል ሚዲያ ዘርፍ የተለያዩ ሰፋፊ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑ ይታወቃል።
ኢኒሼቲቩ ወጣቶች አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እንዲያውቁና በዲጂታል ዘርፍ ክህሎታቸውን እንዲያሳድጉ መሠረት ጥሏል
Nov 30, 2025 142
አዲስ አበባ፤ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፡-የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እንዲያውቁና በዲጂታል ዘርፍ ክህሎታቸውን እንዲያሳድጉ መሠረት እንደጣለላቸው ወጣቶች ገለጹ፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ይፋ የተደረገው የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና የሚወስዱበት ሂደት ነው፡፡ በኢትዮጵያ እየተንቀሳቀሱ የሚገኙ ስታርትአፖች በሀገሪቱ ፈጣን ዕድገት ለማምጣት እና ገበያውን ለመለወጥ የተያዘውን ጥረት በእጅጉ እያገዙ ይገኛሉ፡፡ ይህን ተከትሎ በርካታ ስታርታፖች በቴክኖሎጂ በመታገዝ በሚሰሯቸው ስራዎች የፋይናንስ አገልግሎቶች፣ የግብርና ቴክኖሎጂ እንዲሁም የሎጂስቲክስና የኢ-ኮሜርስ ዘርፎች በስፋት ተደራሽ እንዲሆኑ እያስቻሉ ነው፡፡ ኢዜአ ያነጋገራቸው ስታርታፖች ኢኒሼቲቩ የዲጂታል አቅማቸውን በማጎልበት ተጨማሪ ክህሎት እንዲጨብጡ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ የአዲስ ኤ አይ ድርጅት መስራች ወጣት ቃልኪዳን ደምሌ፤ በቴክኖሎጂው ዘርፍ በመሰማራት ውጤታማ ስራዎችን ለማበርከት የወሰደችው የኮደርስ ስልጠና በሚገባ እንደጠቀማት ተናግራለች፡፡ በሁለት የሀገር ውስጥ ቋንቋዎች የሚሰራ መተግበሪያ በመፍጠር ወደ ስራ ማስገባት መቻሏን የምትናገረው ወጣቷ ለዚህ ስኬትም ስልጠናውን መውሰዷ እንደረዳት ገልጻለች፡፡ ስልጠናው በተለይም በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳደሪ ለመሆን፣ ፈጠራን ለማላቅ ብሎም የሥራ ዕድሎችን ለማግኘት እንዳስቻላት ጠቅሳለች፡፡ ያሬድ እንዳለ በበኩሉ መንግስት እያደረገላቸው በሚገኘው ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ከራሳቸው አልፈው ለበርካቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ተናግሯል፡፡ የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ወጣቶች አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እንዲያውቁና በዲጂታል ዘርፍ ክህሎታቸውን እንዲያሳድጉ መሠረት መጣሉን ጠቅሷል፡፡ ይህም ስታርታፖች በቴክኖሎጂው ዘርፍ ራሳቸውንና ሀገራቸውን የሚለውጡ የፈጠራ ስራዎችን እንዲያበረክቱ ዕድል መፍጠሩን ተናግሯል፡፡ የፌዶ ፓወር ሶሉሽን ድርጅት ባለቤት ወጣት ፌደሳ ሹማ በበኩሉ በፈጠራ ውጤቱ በመታገዝ ችግር ፈቺ ስራዎችን በመሥራት ላይ እንደሚገኝ ተናግሯል፡፡ የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ስራው ለማሳደግ የሚረዳውን ተጨማሪ ዕውቀት በማስጨበጥ ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን እንዳስቻለው ገልጿል፡፡
የካዳስተር ቴክኖሎጂ ዘመናዊ የከተማ መሬት አስተዳደርና የውሳኔ አሰጣጥ አቅምን እያጎለበተ ነው - ሚኒስቴሩ
Nov 29, 2025 134
አዲስ አበባ፤ ህዳር 20/2018(ኢዜአ)፦ የካዳስተር ቴክኖሎጂ ዘመናዊ የከተማ መሬት አስተዳደርና የውሳኔ አሰጣጥ አቅምን እያሳደገ መሆኑን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ገለጹ፡፡ ሚኒስትር ዴኤታው ለኢዜአ እንዳሉት፤ የካዳስተር መረጃ የከተሞችን የመሬት ሃብት በዘመናዊ አሰራር ሥርዓት ለመምራት ወሳኝ ነው፡፡ ባለፉት ሶስት ዓመታት ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የኢትዮጵያን የመሬት ገጽታ በካዳስተር ሥርዓት ማደራጀት የሚያስችል ስኬታማ ተግባር መከናወኑን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ ከተሞች ወሰኑ በምድርና በካርታ ላይ በግልጽ ተለይቶ የመጠቀም መብት የተረጋገጠለት ልዩ የመለያ ኮድ ያለው ስድስት ነጥብ ስድስት ሚሊየን ቁራሽ መሬት ወይም ነጠላ የመሬት ይዞታ እንደሚገኝ ተናግረዋል። እስካሁንም በ150 ከተሞች ከሁለት ሚሊዮን በላይ ቁራሽ መሬት በካዳስተር ተመዝግቧል ብለዋል፡፡ የካዳስተር ቴክኖሎጂ መልክዓ-ምድራዊ የመረጃ ከተሞች ተዓማኒ፣ ትክክለኛና የተናበበ የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም እንዲኖራቸው እያደረገ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የካዳስተር ቴክኖሎጂ የከተማ መሬትን ለሚፈለገው የልማት ዓላማ እንዲውል በማስቻል የዜጎችን ፍትሕዊ የይዞታ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ማድረግ ያስችላል ብለዋል፡፡ የካዳስተር ቴክኖሎጂ ምዝገባ ሥርዓት በዕቅድ የሚመሩ ዘመናዊና የገቢ አቅማቸው ያደገ ከተሞች እንዲፈጠሩ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። በጥናት ላይ የተመሰረተ የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማት ግንባታዎችን በማሳለጥ የከተሞችን ዕድገት እያፋጠነ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት የአየር ላይ ቅየሳ መሪ ሥራ አስፈፃሚ ከማሁ አብርሃም፤ የአየር ላይ ቅየሳ ቴክኖሎጂ በመጠቀም የኢትዮጵያ የመሬት ገጽታ በካዳስተር እንዲደራጅ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በካዳስተር የቴክኖሎጂ ሥርዓት የተደራጁ የመሬት ገጽታ መረጃዎችን ለውሳኔ ሰጪ አካላት እንዲቀረቡ እየተደረገ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም የመሬት ገጽታን በመለየት በአንድ ቋት መምራት የሚያስችል አቅም ይፈጥራል ብለዋል፡፡ በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ቀሪ የመሬት ገጽታዎችን በካዳስተር ቴክኖሎጂ ሥርዓት አደራጅቶ ለመያዝ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል፡፡
የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እንግልትን አስቀርቶልናል- ተገልጋዮች
Nov 28, 2025 212
ባሕር ዳር ፤ ሕዳር 19/2018(ኢዜአ) ፡- በባሕርዳር ከተማ የተጀመረው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀደም ሲል ሲያጋጥማቸው የቆየውን እንግልት በማስቀረት ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ተገልጋዮች ገለጹ። በአንድ ማዕከል አገልግሎቱ ለደንበኞች በተሰጠ የአገልግሎት እርካታ 95 በመቶ ማድረስ እንደተቻለ በተካሄደ ዳሰሳ ጥናት ማረጋገጥ መቻሉም ተገልጿል። በአማራ ክልል ባሕርዳር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ጉዳይ ሲያስፈፅሙ ኢዜአ ያነጋገራቸው ሃይማኖት ይበልጣል እና ሰለሞን ውበት በሰጡት አስተያየት፤ በማዕከሉ ከእንግልት ነፃ የሆነ ፈጣን አገልግሎት ማግኘት እንደቻሉ ተናግረዋል። በማዕከሉ ከሰራተኞች አቀባበል ጀምሮ መልካም የሚባል አገልግሎት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ቀደም ሲል ማንኛውንም ዓይነት አገልግሎት ለማግኘት ወደ ተቋማት በሚኬድበት ወቅት ፋይል ጠፋ በሚል ለመፈለግ ቀኑን ሙሉ ማሳለፍ ግድ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ላይ በዘመናዊ አሰራር ችግሩን በመፍታት ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘት እንደቻሉ አስረድተዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎቱ ቀደም ሲል ሲያጋጥማቸው የቆየውን እንግልት በማስቀረት ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ተገልጋዮቹ ገልጸዋል። የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በበኩላቸው ፤ ሕዝብ የሚቸግራበችውን አገልግሎቶች በመለየት የማዘመን ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። በባሕር ዳር ከተማ የተጀመረው የአንድ ማዕከል አገልግሎት በ12 ተቋማት 92 አገልግሎቶችን ለመስጠት ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ አሁን ላይ በዘጠኝ ተቋማት 48 አገልግሎቶችን መስጠት እንደተቻለም አስታውቀዋል። የአማራ ክልል ሲቪል ሰርቪስና ሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ባንችዓምላክ ገብረማርያም፤ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የመንግስት አስተዳደር ሪፎርምና የዲጂታል ኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ አካል ሆኖ እየተተገበረ ነው ብለዋል። የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሰጣጡ የመንግስትንና የሕዝብን ትስስርን ይበልጥ በማጠናከር የመልካም አስተዳደርና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታተ በጥናት ተለይቶ የተገባበት ተግባር መሆኑን አንስተዋል። በክልሉ አራት የፌደራልና አስር የክልል ተቋማት 54 አገልግሎቶችን እየሰጡ ሲሆን፤ በአንድ ወር ተኩል ጊዜ ውስጥ ከ10 ሺህ 400 በላይ ደንበኞችን ማስተናገድ እንደተቻለም አስረድተዋል። ከደንበኞች በተደረገ የዳሰሳ ጥናትም የአገልግሎት እርካታውን 95 በመቶ ማድረስ መቻሉም ተረጋግጧል ብለዋል።
ቴክኖሎጂን በመጠቀም ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Nov 28, 2025 189
አዲስ አበባ፤ ህዳር 19/2018(ኢዜአ)፦ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ገለጸ፡፡ የመስሪያ ቤቱ ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ መስሪያ ቤቱ የሀገሪቱን ውስን ሀብትና ንብረት ከብክነት ለማዳን እንዲሁም ብልሹ አሠራሮችን የመከላከል ተልዕኮውን አጠናክሮ መቀጠሉንም ተናግረዋል፡፡ በዚህም የፌዴራል መስሪያ ቤቶች የተበጀተላቸውን በጀት ለታለመለት ዓላማ ማዋላቸውን ኦዲት በማድረግ በማረጋገጥ ላይ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በዚህም ፋይናንሻል ኦዲት፣ ክዋኔ ኦዲት፣ ልዩ ኦዲትን ጨምሮ በሌሎችም ጉዳዮች የኦዲት ስራ በመከናወን ላይ እንሚገኙ ገልጸዋል፡፡ መስሪያ ቤቱ ተጠያቂነትን ለማስፈንም ከገንዘብ ሚኒስቴር፣ ከፍትህ ሚኒስቴር እና ከስነ ምግብርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን ዋና ኦዲተሯ ጠቅሰዋል። እንደ ኦዲት ግኝቱም መሸለም የሚገባቸው ተቋማት የሚሸለሙበትና ተጠያቂ የሚሆኑ ተቋማት የሚጠየቁበት አሠራር መዘርጋቱን ተናግረዋል፡፡ በኦዲት ግኝቱ መሠረት ከኃላፊነታቸው የተነሱና ተጠያቂ የሆኑ አመራሮች መኖራቸውን ለአብነት አንስተው፤ ከለውጡ ወዲህ የክዋኔ ኦዲት ቁጥርና የክትትል አቅም እየጨመረ መምጣቱን ጠቁመዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ ዲጂታል አሠራር ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲኖር፣ የገንዘብ ንክኪን ለማስቀረት እንዲሁም የአሠራር ስርዓትን በማዘመን ሙስናን ለመከላከል ፋይዳው የጎላ ነው ብለዋል። ይህም ሙስናና ብልሹ አሠራሮችን ለመቆጣጠር ትልቅ ጠቀሜታ ያለው መሆኑን ጠቁመው፤ ወቅቱ የሚፈልገውና ዓለም እየሄደበት ያለው አቅጣጫ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ መስሪያ ቤቱም አሠራሩን ለማዘመን ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ጋር እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።
ስልጠናው በፈጠራ የታገዘ ተግባራትን ለማከናወን አግዞናል - የኮደርስ ሰልጣኞች
Nov 28, 2025 137
ወልዲያ፤ ሕዳር 19/2018(ኢዜአ)፡- በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የተመቻቸላቸውን ዕድል በመጠቀም በፈጠራ የታገዘ ተግባራትን ለማከናወን እንዳገዛቸው በሰሜን ወሎ ዞን የኮደርስ ሰልጣኞች ገለጹ። የ "አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ" ስልጠና ኢንሼቲቭ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ይፋ የተደረገ የዲጂታል ክሕሎት ማሳደጊያ መረሃ ግብር ነው። "ትውልድ ይማር፣ ይሰልጥን ፣ ከዓለም ጋር ይፎካከር" በሚል እሳቤ መርሃ ግብሩ በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች እየተካሄደ ሲሆኑ፤ ከእነዚህም በአማራ ክልል የሰሜን ወሎ ዞን ይገኝበታል። በሰሜን ወሎ ዞን ባለፉት አራት ወራት ከሁለት ሺህ በላይ ወጣቶችና ሌሎች የሕብረተሰብ ክፍሎች የኮደርስ ስልጠናን በብቃት በማጠናቀቅ የማረጋገጫ ሰርቲፊኬት መውሰዳቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታውቋል። ስልጠናውን ካጠናቀቁት መካከል የዞኑ የመንግሰት ኮሙኒኬሽን መምሪያ ባለሙያ የሆኑት ታደሰ አብዬ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ስልጠናው በፈጠራ የታገዘ ተግባራትን ለማከናወን አቅም ፈጥሮልኛል ብለዋል። በተለይ የኮምፒውተር ስራን አቅልሎ ለመስራትና ከወረቀት የተላቀቀ ዲጂታላይዜሽን አሰራርን መተግበር የሚያስችል እውቀት እንዳገኙበት ተናግረዋል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የአገልግሎት አስጣጥን የሚያቀላጥፍ ነው ያሉት ደግሞ ሌላው ሰልጣኝ አቶ ሰለሞን አሰፋ ናቸው። ስልጠናው ሁለት ወራት እንደወሰደባቸው ጠቅሰው፤ ቀደም ሲል ያላወቅኳቸውን የመረጃ አያያዝና ሌሎች ዕውቀቶችን እንዳገኝ አግዞኛል ብለዋል። ስልጠናው ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠትና የመልካም አስተዳደርን ማስፈን የሚያስችል በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም አመልክተዋል። በሰሜን ወሎ ዞን አስተዳደር የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ቡድን መሪ አማኑኤል ሮብሶ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ሕብረተሰቡን በተለይም ወጣቱን በኮደርስ ስልጠና ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው። የመርሃ ግብሩ ዓላማ ወጣቱ ትውልድ እንዲሁም አመራሩና ሠራተኛው በዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ መሳተፍ የሚያስችላቸውን የዲጂታል ክህሎት እንዲኖራቸው ለማመቻቸት እንደሆነ ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱም ከ25ሺህ በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በኮደርስ ለማሰልጠን ታቅዶ በተደረገ ጥረት በአራት ወራት ውስጥ ከሁለት ሺህ በላይ ማሰልጠን መቻሉን አስታውቀዋል። በፕሮግራሚንግ ልማት፣ በዳታ ሳይንስ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግና በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ ከህሎትን ለማስጨበጥ የተሰጠውን ስልጠና ላጠናቀቁ ሰርትፍኬት እንዲያገኙ መደረጉን ተናግረዋል። በቀሪ ወራትም የስልጠና ማዕከላትን በማስፋት የታቀደውን ለማሳካት ሁሉን አቀፍ ጥረት እንደሚደረግ ገልጸዋል። ለስልጠናው ስኬት በዞንና በወረዳ የሚገኙ የአይ ሲቲ ማዕከላት፣ የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ኮሌጆች፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችና የወልዲያ ዩኒቨርሲቲ አይሲቲ ማዕከላት አገልግሎት እየሰጡ መሆኑም ተመልክቷል።
በኢትዮጵያ የኢንተርፕርነር ምሕዳሩን ለማስፋት የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Nov 27, 2025 235
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 18/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የኢንተርፕርነር ምሕዳሩን ለማስፋት የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል አስታወቁ። "በጋራ እንገንባ" በሚል መሪ ሀሳብ በተለያዩ መርሃ ግብሮች ሲካሄድ የቆየው ዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሺፕ ሳምንት ዛሬ ተጠናቋል። ተቀማጭነቱን አሜሪካን ሀገር ያደረገው ግሎባል ኢንተርፕርነርሺፕ ኔትወርክ፤ ኢትዮጵያ በሀገር አቀፍ ደረጃ ባዘጋጀቻቸው ኹነቶች ከ200 ሀገራት ጋር ተወዳድራ አንደኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን ገልጿል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት በማጠቃለያ መርሃ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትሯ ሙፈሪሃት በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የኢንተርፕርነር ምህዳር ግንባታ ላይ የተከናወኑ ስራዎች በዘርፉ ውጤት እንዲመዘገብ አድርጓል። በአሁኑ ወቅት በኢንተርፕርነር ዘርፉ ላይ የተገኘው ስኬት የኢትዮጵያን አዲስ መልክና እድገት ለማስተዋወቅ የሚረዱ መሆናቸውንም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በ2017 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ውድድር በማድረግ ከዓለም ስምንተኛ ከአፍሪካ ደግሞ ሁለተኛ በመሆን አጠናቅቃ እንደነበርም አስታውሰዋል። በዘንድሮው ዓመትም በርካታ ተቋማት በመደመር እሳቤ በዘርፉ በትብብር መስራታቸው ኢትዮጵያ ቀዳሚውን ስፍራ በመያዝ ውድድሩን እንድታጠናቅቅ አድርጓል ነው ያሉት። በአጭር ጊዜ ውስጥ የኢንተርፕርነር ዘርፍ ምህዳርን በማስፋት ለውጥ እንዲመጣ ማድረግ ተችሏል ያሉት የሥራና ክህሎት ሚኒስትሯ፤ በቅንጅት ከተሰራ የኢትዮጵያን እድገት ለማሳካት እንደማያዳግትም አመላካች መሆኑን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በውድድሩ ያስመዘገበችው ውጤት ኢንቨስትመንትን ከመሳብ ባሻገር ችግር ፈቺ ኢንተርፕርነሮችን እና በዘርፉ ምርምር የሚያደርጉ አካላትን ለማፍራት እንደሚረዳ አብራርተዋል፤ የኢንተርፕርነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሀሰን ሁሴን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በዘንድሮው ዓመት ኢንተርፕነር ዘርፉን ለመለወጥ በጋራ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት አምጥተዋል። ይህንን ጥረት በማጠናከርም በቀጣይ በተለይ የዘርፉን ምህዳር የማስፋት ስራን ስኬታማ ለማድረግ ባለድርሻ አካላት በቅንጅት መስራት እንዳለባቸውም ነው ጥሪያቸውን ያስተላለፉት ።
ኢትዮ ቴሌኮም ሶስተኛውን የኤሌክትሪክ መኪና ባትሪ መሙያ ጣቢያ አገልግሎት አስጀመረ
Nov 27, 2025 185
አዲስ አበባ፤ ህዳር 18/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮ ቴሌኮም ሶስተኛውንና እጅግ ፈጣን የሆነውን የኤሌክትሪክ መኪና ባትሪ መሙያ ጣቢያ አገልግሎት በአዲስ አበባ አስጀምሯል። ኢትዮ ቴሌኮም በአዲስ አበባ ሰሚት በተለምዶ ፍየል ቤት አካባቢ ያስገነባውን ሶሰተኛውን ዘመናዊና ፈጣን የኤሌክትሪክ መኪና ባትሪ መሙያ ጣቢያ አገልግሎት አስጀምረዋል። በዚሁ ወቅት የኢት ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ እንዳሉት ጣቢያው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ መጠቀምን የሚያበረታታና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የተጀመረው ጥረት አንዱ አካል ነው። ኢትዮ ቴሌኮም ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ከማድረግ በተጨማሪ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ላይ የበኩሉን አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ገልፀው፤ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ባትሪ መሙያ ጣቢያ ግንባታ የዚሁ አካል መሆኑን ጠቅሰዋል። የባትሪ መሙያ ጣቢያው የተገጠመለት ቴክኖሎጂ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀና አስተማማኝ መሆኑን ጠቁመዋል። እንዲሁም በሰው ሰራሽ አስተውሎት(AI) ቴክኖሎጂ የባትሪ መስፈርቶችን በመተንተን እንዲሁም የባትሪውን ደህንነት በመፈተሽ የተሽከርካሪውን ባትሪ በፍጥነት ቻርጅ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል። ከዚህ በፊት ተቋሙ በተከላቸው ሁለት የባትሪ መሙያ ማዕከላት ከ165 ሺህ በላይ ተሽከርካሪዎች የኤሌክትሪክ ቻርጅ መጠቀማቸውን ጠቁመዋል። ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያው በአንድ ጊዜ 16 ተሽከርካሪዎች ባትሪ እንዲሞሉ የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰው፤ አንድ መኪና በ15 ደቂቃ ባትሪውን መሙላት እንደሚችል ተናግረዋል።
ምክር ቤቱ በአራተኛ መደበኛ ስብሰባው እንዲፈፀሙ ያስቀመጣቸውን ተግባራት አፈፃፀም በጥልቀት በመገምገም አቅጣጫ አስቀምጧል - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስተር ተመስገን ጥሩነህ
Nov 26, 2025 637
የብሔራዊ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ምክር ቤት በአራተኛ መደበኛ ስብሰባው እንዲፈፀሙ ያስቀመጣቸውን ተግባራት አፈፃፀም በጥልቀት በመገምገም አቅጣጫ ማስቀመጡን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስተር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት የብሔራዊ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ምክር ቤት በዛሬው ዕለት አምስተኛ መደበኛ ስብሰባውን ማካሄዱን አስታውቀዋል። ምክር ቤቱ በአራተኛ መደበኛ ስብሰባው እንዲፈፀሙ ያስቀመጣቸውን ተግባራት አፈፃፀም በጥልቀት በመገምግሞ አቅጣጫ አስቀምጧል ነው ያሉት። ምክር ቤቱ አጠቃላይ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን የስራ ክንውን፣ የዲጂታል መታወቂያ የምዝገባ ሂደት እንዲሁም ‘የ5 ሚሊየን የኢትዮጵያ ኮደርስ’ ኢኒሼቲቭ ትግበራ አፈጻጸምን ገምግሞ በቀጣይ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ከስምምነት ላይ ደርሷል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአገራችን በመከናወን ላይ የሚገኙ እንዲሁም አዳዲስ የዲጂታል ሰራዎች ከዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ ጋር ያላቸውን ተጣጣሚነትን በውይይታችን ዳሰናል ብለዋል። በመጨረሻም ምክር ቤቱ ረቂቅ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ላይ ጥልቅ ውይይት ካደረገ በኃላ ስትራቴጂ ሰነዱን በማፅደቅ ወደ ሚኒስትሮች ምክር ቤት እንዲላክ ወስኗል ነው ያሉት። የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታችን በእመርታ የሚያድግበት ዘመን ላይ እንደመሆኑ፤ ምክር ቤቱም ለዚሁ ዕድገት ተገቢውን ሚና ለመወጣት የጀመረውን ጥረት አጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉም አስታውቀዋል፡፡
በመናኸሪያው የተጀመረው የኢ-ቲኬቲንግ አገልግሎት እንግልትን አስቀርቷል
Nov 26, 2025 156
ሆሳዕና፤ ህዳር 17/2018(ኢዜአ)፦ በሆሳዕና ከተማ በህዝብ መናኸሪያ የተጀመረው የኢ-ቲኬቲንግ አገልግሎት በተሳፋሪ ላይ ሲደርስ የነበረን ያልተገባ የዋጋ ጭማሪና እንግልት ማስቀረቱን ተገልጋዮች ገለጹ። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ በበኩሉ ለህዝብ የሚሰጠው የትራንስፖርት አገልግሎት ዲጂታላይዝ ለማድረግ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል። መንግስት የትራንስፖርት ዘርፉን ማነቆዎች በመፍታት በህዝቡ የሚነሱ የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስና የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው። በዚህም በዲጂታል የታገዘ የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት በህዝብ መናኸሪያዎች የኢ-ቲኬቲንግ አገልግሎት በማስጀመሩ ለውጥ እየተመዘገበ መጥቷል። ኢዜአ በሆሳዕና ከተማ የህዝብ መናኸሪያ ተገኝቶ ያነጋገራቸው ተሳፋሪዎችና አሽከርካሪዎች በመናኸሪያው የኢ-ቲኬቲንግ አገልግሎት ትርፍ ሰው ከመጫንና ተጨማሪ ክፍያን በማስቀረት በተሳፋሪ ላይ ሲደርስ የነበረን እንግልት ማስቀረቱን ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ ወንድም ዳኜ እንደገለጹት ፤ ከዚህ ቀደም በመናኸሪያው ትርፍ መጫንና ማስከፈልን ጨምሮ የተለያዩ እንግልቶች ይገጥሙ ነበር። በዲጂታል የተደገፈ አገልግሎት መስጠት ከተጀመረ ወዲህ ከትራንስፖርት አገልግሎቱ ጋር በተያያዘ ቀደም ሲል ሲገጥሙን የነበሩ ችግሮች ተፈተዋል፤ አሰራሩም በቀጣይ መጠናከር አለበት ብለዋል። አቶ አየለ ጊፊሶ የተባሉ ተሳፋሪ በበኩላቸው እንዳሉት በመናኸሪያው የተጀመረው የኢ-ትኬቲንግ አገልግሎት ተገቢ ያልሆነ ክፍያን ከማስቀረት ባለፈ በተሳፋሪ ላይ ሲደርስ የነበረን እንግልት አስቀርቷል። ይሁንና የዲጂታል አገልግሎቱ በወረዳ ባሉ መናኸሪያዎች ባለመጀመሩ ከታሪፍ ውጭ ማስከፈል አሁንም እንዳለ ጠቅሰው ዲጂታል ትራንስፖርት አገልግሎቱ በሁሉም መዋቅሮች እንዲስፋፋ ጠይቀዋል፡፡ መንግስት ባስቀመጠው የታሪፍ ክፍያ መሰረት ማህበረሰቡን እያገለገሉ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በመናኸሪው የህዝብ ትራንስፖርት አሽከርካሪው ግዛቸው ሃይሉ ናቸው። የኢ-ቲኬቲንግ መጀመር ከተራ አስከባሪዎች ጋር የነበራቸውን ያለመግባባት ችግር መፍታቱን ተናግረዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ መሀመድ ኑርዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በክልሉ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎትን ዲጂታላይዝ በማድረግ የተመዘገበውን ውጤት ለማጠናከር ይሰራል ብለዋል። የኢ-ቲኬቲንግ አገልግሎት በክልሉ በሚገኙ 23 መናኸሪያዎች ተግባራዊ መደረጉንም ተናግረዋል፡፡ አገልግሎቱ በትራንስፖርት ዘርፍ የነበሩ ብልሹ አሰራሮችን ከመቀነስ አኳያ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰው፣ በቀጣይም አገልግሎቱን በሁሉም መናኸሪያዎች የማስፋት ሥራ ይሰራል ብለዋል።
በሐረሪ ክልል ሰባት ሺህ 500 ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት ወስደዋል
Nov 25, 2025 187
ሐረር፤ ህዳር 16/2018 (ኢዜአ):- በሐረሪ ክልል እስካሁን ሰባት ሺህ 500 ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት መውሰዳቸውን የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ አስታወቀ። የኤጀንሲው ኃላፊ አቶ ጀማል ኢብራሂም ለኢዜአ እንደገለፁት በክልሉ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እስካሁን 16 ሺህ ዜጎች ስልጠናውን ወስደዋል። ስልጠናውን ከወሰዱት መካከል እስካሁን ሰባት ሺህ 500 ዜጎች በብቃት በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት መውሰዳቸውን ተናግረዋል። በክልሉ በተያዘው በጀት ዓመት ከ15 ሺህ በላይ ወጣቶችን የስልጠናው ተጠቃሚ ለማድረግ መታቀዱን የገለጹት አቶ ጀማል፤ ባለፉት አራት ወራት ከ6 ሺህ 500 በላይ ወጣቶችን በዘርፉ ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ፕሮግራሚንግ፣ ዳታ ሳይንስ፣ አንድሮይድ፣ ሰው ሰራሽ አስተውሎትና ተያያዥነት ያላቸው ስልጠናዎች እየተሰጡ እንደሚገኙም ገልጸዋል። ሥልጠናው ወጣቶችን የክህሎት ባለቤት ከማድረግ ባለፈ ብቁ፣ ተወዳዳሪና ስራ ፈጣሪ እንዲሆኑ እያስቻለ መሆኑንም አክለዋል። የአምስት ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መርሃ ግብር በክልሉ በታቀደው መሰረት እየተከናወነ እንደሚገኝም አመልክተዋል፡፡ በክልሉ ስልጠናውን ያልወሰዱ ወጣቶች በቀጣይ ጊዜያት ተመዝግበው እንዲሰለጥኑና የእድሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑም ኃላፊው ጥሪ አስተላልፈዋል። የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና ወጣቶችን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እያደረገ መሆኑም ይታወቃል።
የጤና አገልግሎት ጥራትን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የምርምር ስራዎች ላይ ሊያተኩሩ ይገባል
Nov 24, 2025 439
አምቦ፤ ሕዳር 15/2018(ኢዜአ)፦ የጤና አገልግሎት ጥራትን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የጥናትና ምርምር ስራዎች ላይ ማተኮር እንዳለባቸው የጤና ዘርፍ መምህራን አመለከቱ። የጤና ትምህርት አሰጣጥን በማዘመን ብቁና ተወዳዳሪ ባለሙያ ማፍራት ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በአምቦ ዩኒቨርሲቲ ተካሄዷል። በመድረኩ ላይ የተሳተፉት የአምቦ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ረዳት ፕሮፌሰር ሙሉ ኪታባ፣ ጥራት ያለው የጤና አገልግሎትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ በዘርፉ ብቁና ተወዳዳሪ የሰው ሀይል ማፍራት አስፈላጊ ነው ብለዋል። ለተግባራዊነቱም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የሰው ሀይል ለማፍራት በተግባር የተደገፈ የጥናትና ምርምር ስራዎችን ማካሄድ እንዳለባቸው አስረድተዋል። የጤና ትምህርት አሰጣጥን ማዘመን መንግስት ተግባራዊ ያደረገውን የበሽታ መከላከልና አክሞ የማዳን የጤና ስራ ለማሳካትም መሰረት መሆኑን ተናግረዋል። በአምቦ ዩኒቨርሲቲ አዘጋጅነት የተካሄደው የምክክር መድረክም የዚሁ አካል መሆኑን ጠቅሰው የአምቦ ዩኒቨርሲቲም የጤና ትምህርት አሰጣጥን በጥናትና ምርምር በማስደገፍ ከዘመኑ ጋር ማጣጣም ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በተለይም አምቦ፣ ጅማ እና የኖርዌይ ቪ.አይ.ዲ ዩኒቨርሲቲ በጋራ የጤና ዘርፍ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ዲግሪ ተማሪዎች የሚያደርጉትን የጥናትና ምርምር ስራዎች የህብረተሰቡን ችግር በተጨባጭ እንዲፈቱ የማማከር ስራዎችን በጋራ ያከናውናሉ ብለዋል። በጅማ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ረዳት ፕሮፌሰር አበበ አበራ በበኩላቸው፤ የጤና ትምህርትን ውጤታማ ለማድረግ የምሁራን እና ባለድርሻ አካላት ትብብር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በአምቦ ዩኒቨርሲቲ አዘጋጅነት የተካሄደው የምክክር መድረክም የጤና ትምህርት አሰጣጡን በተግባር በማስደገፍና የጥናት እና ምርምር ስራዎች የህብረተሰቡን ችግር የሚፈቱ የፖሊሲ ሀሳቦች እንዲሆኑ የሚያግዝ መሆኑን ጠቅሰዋል። የኖርዌይ ቪ.አይ.ዲ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ ተስፋዬ ለታ (ዶ/ር)፤ የጤና ትምህርት አሰጣጥን ወቅቱ በደረሰበት ዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍ መሰጠቱ ብቁና ተወዳዳሪ የጤና ባለሙያ ለማፍራት እንደሚያግዝ ገልጸዋል። በዚህም ዩኒቨርሲቲዎቹ የጀመሩት ትብብር ዘርፉን ለማሻሻል በጎ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል።