ሳይንስና ቴክኖሎጂ
በክልሉ የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት ችግር ፈቺ የቴክኖሎጂና የምርምር ሥራዎችን ሊያጠናክሩ ይገባል
Apr 30, 2025 30
ቦንጋ፤ሚያዚያ 22/2017 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የሚገኙ የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ የቴክኖሎጂና ምርምር ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚገባቸው ተገለፀ። የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ ''ብሩህ አዕምሮዎች፣ በክህሎት የበቁ ዜጎች'' በሚል መሪ ቃል የክህሎት፣የቴክኖሎጂና የተግባራዊ ጥናትና ምርምር ውድድርና አውደ ርዕይ በቦንጋ ከተማ ማካሄድ ጀምሯል። የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ ወንድሙ ኩርታ በወቅቱ እንደገለጹት፣ በክልሉ የሚገኙ የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት በቴክኖሎጂና ምርምር ዘርፍ የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ ሥራዎችን ማፍለቅ ይጠበቅባቸዋል። ይህን እውን ለማድረግም ለተቋማቱ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል ። ተቋማቱ በስነምግባር የታነፀ የፈጠራ ክህሎት ያለው የሰው ኃይል በማፍራትና ዘርፉ ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር፣የቴክኖሎጂ ሽግግር የሚያደርግበትን አቅም መፍጠር ላይ ተጨማሪ ስራ መስራት እንደሚጠይቅም አመልክተዋል። የቴክኒክና ሙያ ማስልጠኛ ተቋማቱ የክልሉን የልማት ጸጋ ማዕከል ያደረገ ብቁ የሰው ሀይል ማፍራትና ቴክኖሎጂን መቅዳት ላይ አተኩረው እንዲሰሩ የሚደረገው ጥረት እንደሚጠናከር የተናገሩት ደግሞ የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አብይ አንደሞ ( ዶ/ር) ናቸው። የክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራን ዘላቂና አስተማማኝ ለማድረግ ከስልጠና በተጨማሪ በምርምር አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራ ጠቁመዋል። የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊና የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ኃላፊ ወይዘሮ ቤቴልሔም ዳንኤል በበኩላቸው፥ በክልሉ የሚካሄደው ሁለተኛ ዙር የክህሎት፣ቴክኖሎጂና የተግባራዊ ጥናትና ምርምር ውድድርና አውደርዕይ የትምህርት ተቋማቱ በክህሎት፣በቴክኖሎጂና በፈጠራ ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋን ለማፍራት የሚያደርጉትን ጥረትን የሚያግዝ ነው። ለሁለት ተከታታይ ቀናት በሚቆው ውድድር በቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች የተሰሩ የተለያዩ የቴክኖሎጂ፣የፈጠራ እና የምርምር ስራዎች የቀረቡ ሲሆን አሸናፊ ለሚሆኑት ማበረታቻ ሽልማትና ዕውቅና እንደሚሰጥ ታውቋል።
በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ልማት ሽግግርን የሚያሳልጥ ምቹ የአሰራር ምህዳር ተፈጥሯል -የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር
Apr 30, 2025 42
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ልማት ሽግግርን የሚያሳልጥ ምቹ የአሰራር ሥርዓተ ምህዳር መፈጠሩን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በኢትዮጵያ ቁልፍ የልማት ዘርፎች ላይ የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግርን የማሳለጥ ዓላማን ያነገበ የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ አካሂዷል።   የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) በመድረኩ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር እንደገለጹት፤ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ልማትን ለማሳለጥ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል። የዲጂታል ቴክኖሎጂ ልማትን ለማስፋትም ከተቋማት ጋር በመተባበር በመንግስትና የግል አጋርነት ጭምር ቀጣይነት ያላቸው ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፥ የዜጎችን የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎት ለማበልጸግ ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘው የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠናም ወሳኝ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝም ተናግረዋል። ዜጎችም በአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና ላይ በንቃት በመሳተፍ የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎታቸውን ማበልጸግ የሚችሉበትን ዕድል መጠቀም እንዳለባቸው መልዕክት አስተላልፈዋል። የቴክኖሎጂ አቅም የመምራት፣የማቀናጀትና የመገንባት መሪነት ሚና በመወጣት ስኬታማ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ልማትና ሽግግር ሥነ-ምኅዳር መፍጠር እንደተቻለም ተናግረዋል። በዚህም በስታርት አፕ፣በሰው ሃብት ልማት፣ በፖሊሲ የሕግ ማዕቀፍ ዝግጅትና አሰራር የመሰረተ ልማት ዝርጋታ ምቹ የቴክኖሎጂ ሽግግር ልማት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። ባለፉት ሰባት ዓመታትም በቴክኖሎጂ ልማት ሽግግር የተከናወነው ተግባራት ከሀገር በቀል እስከ ዓለም አቀፍ ድረስ ዕውቅና የተቸራቸው ስራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል።   በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ክፍል መሪ ስራ አስፈፃሚ ተክለማርያም ተሠማ(ዶ/ር) በበኩላቸው፥ በኢትዮጵያ የ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ በሁሉም መስክ ሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ትኩረት ተሰጥቶታል። በዚህም ሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግርን ማሳለጥ የሚያስችል ፖሊሲን በመተግበር ምርታማነትን ማሻሻል የሚያስችሉ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር የተከናወነው ተግባርም በግብርና፣በጤና፣ በትምህርትና ሌሎች መስኮች የምርታማነትና የአገልግሎት መሻሻል እየተመዘገበ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   በባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዮት የቴክኖሎጂ ኢንኩቤሽንና ኮመርሻላይዜሽን መሪ ሥራ አስፈፃሚ ዑስማን ኡመር፤ የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግርን ለማሳለጥ ከግሉ ዘርፍ፣ ከከፍተኛ ትምህርትና የምርምር ተቋማት ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዚህም በግብርና፣በኢንዱስትሪ፣ ጤናን ጨምሮ በርካታ የቁስና ተፈጥሮ ሳይንሱን በማሰናሰል በባዮ ቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ላይ ቀጣይነት ያለው ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎታችንን እንድናዳብር አስችሎናል - ሰልጣኞች
Apr 30, 2025 57
ሐረር፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎታቸውን ማዳበር እንዳስቻላቸው በሐረሪ ክልል የዘርፉ ሰልጣኞች ገለጹ። የኢትዮ ኮደርስ ዲጂታል ስልጠና በተቀናጀ መልኩ መከናወኑ ውጤት ማስገኘቱን የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ አስታውቋል።   የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የወሰዱ ወጣቶች ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዲጂታል ዘመኑ ራሳቸውን ብቁ በማድረግ ተወዳዳሪ ለመሆን አግዟቸዋል።   ስልጠናውን ከተከታተሉ መካከል ሳምራዊት ዓለሙ እንደገለጸችው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ክህሎቷን አሳድጎላታል። ስልጠናው በመረጃ ራሷን ለማበልጸግ እንዳገዛትም ተናግራለች።   የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናው የቴክኖሎጂ ክህሎትን ለማዳበር እንደረዳት የገለጸችው ደግሞ ሌላዋ ሰልጣኝ ተማሪ ሱመያ አስክንድር ናት። ስልጠናው በቴክኖሎጂ የበቃ ወጣትን ለመፍጠር አጋዥ በመሆኑ ወጣቶች መንግስት ያመቻቸውን እድል በአግባቡ መጠቀም እንዳለባቸውም መክራለች።   የሐረሪ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ ሃላፊ አቶ ጀማል ኢብራሂም በበኩላችው በክልሉ የኢትዮ ኮደርስ በሶስት ዓመት 27ሺህ ወጣቶች ለማሰልጠን ታቅዶ እየተሰራ ነው። በዘንድሮ በጀት አመት ዘጠኝ ወራት ውስጥ በተከናወነ ስራም ከ7ሺህ 300 በላይ ወጣቶች ስልጠናውን መውሰዳቸውን ጠቅሰዋል። ከሰለጠኑት መካከል ከግማሽ በላዮቹ ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው ሰርተፍኬት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። እንደ አቶ ጀማል ገለጻ በክልሉ በትምህርት ቤቶችና በተለያዩ ህዝባዊ መድረኮች ስለ ኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለህብረተሰቡ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ ተከናውኗል። በተጨማሪም ከተለያዩ ተቋማት፣ የግልና የመንግስት ኮሌጆች፣ የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋም ጋር የተፈጠረው ቅንጅታዊ አሰራር ለውጤታማነቱ ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን አስታውቀዋል።   በክልሉ በየደረጃው ያለው አመራር ለኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ትኩረት መስጠቱ ለስኬታማነቱ ተጨማሪ አቅም መሆኑን የገለጹት ደግሞ በኤጀንሲው የኢትዮ ኮደርስ ቴክኖሎጂ አሰልጣኝ አቶ እድሪስ ሰፋ ናቸው። ሰልጣኝ ወጣቶችም በስልጠናው የቴክኖሎጂ ክህሎታቸውን በማዳበር ራሳቸውን ከዲጂታል ዓለም ጋር ለማስኬድ ከወዲሁ መዘጋጀት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።
በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ልማት ሽግግርን የሚያሳልጥ ምህዳር ተፈጥሯል - የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር
Apr 30, 2025 56
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ልማት ሽግግርን የሚያሳልጥ ምህዳር መፈጠሩን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) ገለጹ። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በኢትዮጵያ ቁልፍ የልማት ዘርፎች ላይ የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግርን የማሳለጥ ዓላማን ያነገበ የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ በማካሄድ ላይ ይገኛል። ኢትዮጵያ የስታርት አፕ እና የቴክኖሎጂ ፈጠራ ማዕከል እየሆነች ነው - ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በመድረኩ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) እንዳሉት የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ልማትን ለማሳለጥ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል።   በዚህም በኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ልማትና ግንባታ ሽግግርን የሚያሳልጥ ምህዳር መፈጠሩን አስታውቀዋል። ባለፉት ሰባት ዓመታትም የክህሎትና የፈጠራ ልማትን ለማስፋት የሰው ሃብት ልማት፣ የፖሊሲ ዝግጅትና የአሰራር ሥርዓት በመፍጠር ስኬታማ ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል። የዲጂታል ቴክኖሎጂ ልማትን ለማስፋትም ከተቋማት ጋር በመተባበር በመንግስትና የግል አጋርነት ጭምር ቀጣይነት ያላቸው ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል።   በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዜጎችን የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎት ለማበልጸግ ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘው የ5 ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና ወሳኝ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝም ተናግረዋል። ዜጎችም በ5 ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና ላይ በንቃት በመሳተፍ የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎታቸውን ማበልጸግ የሚችሉበትን ዕድል መጠቀም እንዳለባቸው መልዕክት አስተላልፈዋል። በመድረኩ በባዮ እና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ፣ በስፔስ ሳይንስና ጂኦ-ስፓሻል፣ በቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ከሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ፖሊሲ መስኮች ላይ የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ጉዳዮች ላይ የመነሻ ጽሁፎች ቀርበው ምክክር እንደሚደረግባቸው ተጠቅሷል።
ኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ወጣቶችን ማፍራት የሚያስችል የኢኖቬሽንና የፈጠራ ሥነ ምህዳር እየገነባች ነው - ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Apr 30, 2025 48
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ወጣቶችን ማፍራት የሚያስችል የኢኖቬሽንና የፈጠራ ሥነ ምህዳር እየገነባች መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። "ኢኖቬሽን አፍሪካ 2025" የአፍሪካ የትምህርት፣ አይሲቲ እና ክህሎት የሚኒስትሮች ስብሰባ " በ21ኛው ክፍለ ዘመን አፍሪካን ማስተማርና ማብቃት" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ይገኛል።   የትምህርት፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ እና የሥራና ክህሎት ሚኒስቴሮች ከአፍሪካን ብሬይን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት አህጉራዊ ጉባኤ ዛሬ ይጠናቀቃል። የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ አፍሪካን በትምህርት፣ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ እንዲሁም በክህሎት ልማትና ሥራ ፈጠራ ለማስተሳሰር ያለመ ነው። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል "ለክህሎት ልማትና አዲስ መወዳደሪያ ለአፍሪካ አፍላቂዎች እና ሥራ ፈጣሪዎች" በሚል መሪ ሀሳብ በሚካሄደው የፓናል ውይይት ላይ ንግግር አድርገዋል። ሚኒስትሯ በመክፈቻ ንግግራቸው፤ የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ በኢንዱስትሪዎች፣ ሲቪል ማህበራት፣ በትምህርት ተቋማት መካከል ትብብር በመፍጠር ክህሎትን ለማሳደግ እና የፖሊሲ ግብዓት ለማሰባሰብ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። በአፍሪካ ወጣቶች በስራ ፈጠራ፣ ኢኖቬሽን እና ክህሎት ልማት የላቀ ሚና እንዲኖራቸው ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። የሥራ ፈጠራ ለወጣቶች ከእጅ ወደ አፍ ያለፈ መሆን አለበት ያሉት ሚኒስትሯ፣ አዳዲስ የፈጠራ ክህሎትን ማዳበር ጭምር መሆኑን ተናግረዋል።   በአፍሪካ አካታችና ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት በግብርና፣ ማዕድን፣ ቱሪዝም፣ አይሲቲ ዘርፎች ላይ ክህሎት ማስታጠቅ እና ማብቃት ይገባል ብለዋል። የበለጸገች አፍሪካን ለመገንባት መተባበር እና የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ እና ተጠቃሚነትን ማሳደግ እንደሚገባ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የሀገር በቀል ኢኮኖሚና የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎችን በማድረግ ብልፅግናን ለማረጋገጥ እየሰራች መሆኑን ገልጸዋል። የዓለም የሥራ ፈጠራ ገበያ ውድድር የበዛበት መሆኑን ጠቁመው የወጣቶችን የፈጠራ አቅም ማጎልበትና ማበረታታት ይጠበቅብናል ብለዋል። ኢትዮጵያ በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለበርካታ ወጣቶች የክህሎት ሥልጠና በመስጠት ሥራ ፈጣሪ እንዲሆኑ አስችሏል ነው ያሉት። በዚህም ኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪ እና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ወጣቶችን ማፍራት የሚያስችል አሰራር ስርዓት ተዘርግቶ ተጨባጭ ውጤት አስመዝግባለች ብለዋል። በእያንዳንዱ የቴክኒክ እና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት የክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከላት በማስፋፋት ለወጣቶች ሥራ ፈጠራ ምቹ ሥነ ምህዳር መፍጠር መቻሉን ገልጸዋል።
የበለጸገች አፍሪካን እውን ለማድረግ አካታች የፖሊሲ ማዕቀፍ በማዘጋጀት የወጣቶችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ይገባል - ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር)
Apr 29, 2025 124
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ በቴክኖሎጂ ያደገችና የበለጸገች አፍሪካን እውን ለማድረግ አካታች የፖሊሲ ማዕቀፍ በማዘጋጀት የወጣቶችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚገባ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 የአፍሪካ የትምህርት፣ አይሲቲ እና ክህሎት የሚኒስትሮች ስብሰባ "በ21ኛው ክፍለ ዘመን አፍሪካን ማስተማርና ማብቃት" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው። የትምህርት፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ እና የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአፍሪካን ብሬይን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት አህጉራዊ ጉባኤ ነገ ይጠናቀቃል።   የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ በሪፎርም፣ አቅም ግንባታ፣ የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ሽግግር እንዲሁም ስትራቴጂካዊ ትብብር በመፍጠር የአፍሪካን መፃኢ ጊዜ ለመወሰን ያለመ ነው። "ለኢኖቬሽን እና ትምህርት ሽግግር የዲጂታል ቴክኖሎጂን አቅም መገንባት" በሚል መሪ ሀሳብ ዛሬ የፓናል ውይይት ተደርጓል፡፡ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ የበለጸገችና በቴክኖሎጂ ያደገች ሀገር ለመገንባት ወሳኝ ሁነት ነው። በአፍሪካ የዲጂታል ክህሎት እና የቴክኖሎጂ ፈጠራ አቅምን በማሳለጥ ልማትና እድገትን ለማቀላጠፍ ወጣቶችን የዲጂታል ቴክኖሎጂን ማስታጠቅ ምርጫ ሳይሆን ግዴታ መሆኑን ተናግረዋል። የአፍሪካ ወጣቶች ዓለም አቀፍ ተሳትፎ የሚወሰነው በሚኖራቸው የቴክኖሎጂ አቅም መሆኑን በመግለጽ፤ አካታች ፖሊሲ በመተግበር የዲጂታል ሽግግሩን ማሳለጥ ይገባል ብለዋል፡፡   በአፍሪካ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ የዲጂታል ኢኮኖሚ ለመገንባት የጋራ ጥረት ይጠይቃል ያሉት ሚኒስትሩ፤ ሁሉንም የፈጠራ አቅሞች በመጠቀም ለወጣቶች ምቹ የዲጂታል ሥነ ምህዳር መፍጠር እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ግቧን ያሳካች አፍሪካን እውን ለማድረግ በሁሉም ዘርፍ በትብብር ለመሥራት ቁርጠኝነቷን አጠናክራ ትቀጥላለች ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ኢንጂነሪንግና ሒሳብ ትምህርቶች ለእድገት ወሳኝ መሆናቸውን በመገንዘብ ያልተቋረጠ ጥረት እያደረገች መሆኑንም ገልጸዋል። በመንግስትና የግሉ ዘርፍ የጋራ ጥረት የስታርታፕ እና የቴክኖሎጂ ፈጠራ ኢትዮጵያ ማዕከል እየሆነች ነው ያሉት ሚኒስትሩ፣ በኢንዱስትሪዎች እና ትምህርት ተቋማት መካከል ትብብርን በማዳበር ለስራ ፈጣሪዎች ምቹ ከባቢ እንዲኖር እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የበለጸገች አፍሪካውን እውን ለማድረግ ሁሉንም የኢኖቬሽን አቅም በመጠቀም ለችግሮቻችን መፍትሔ ማበጀት ይገባል ነው ያሉት፡፡   የደቡብ ሱዳን የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ማይክል ማኩይ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ልማት እንደ ኤሌክትሪክ ሀይልና የኢንተርኔት አገልግሎት የሚጠይቅ በመሆኑ ዘርፉን በሚገባ ማሳደግ አልተቻለም ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2012 የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ፖሊሲ በማውጣት እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2024 ወጣቶችን መሰረተ ያደረገ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ስትራቴጂ ተግባራዊ በማድረግ በትክክለኛ ሂደት ላይ ነን ብለዋል፡፡   የማላዊ ኢንፎርሜሽንና ዲጂታላይዜሽን ሚኒስቴር የኢንፎርሜሽን ዳይሬክተር አርቸር ቺፔንዳ በበኩላቸው፤ ከአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ጋር የተጣጣመ ራዕይ እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡ ማላዊ ከሁሉት ዓመት በፊት የማላዊ ብሔራዊ ዲጂታላይዜሽን ፖሊሲ በማጽደቅ ለዘርፉ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች መሆኑን ም ተናግረዋል፡፡ የዲጂታል ስርዓቱን በማቀላጠፍ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ንግድን ለማሳለጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው አስረድተዋል፡፡
በክልሉ በሚቀጥሉት አራት ወራት 50 ሺህ ወጣቶችን በኢትዮ ኮደርስ ለማሰልጠን ይሰራል
Apr 29, 2025 68
ቦንጋ፤ ሚያዝያ 21/2017 (ኢዜአ)፡-በቀጣይ አራት ወራት 50 ሺህ ወጣቶች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለመስጠት እንደሚሰራ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ ሀላፊ አቶ ግዛው ጋግያብ ገለፁ። ቢሮው ለክልሉ ወጣት ክንፍ አመራሮች ስልጠናውን በማስመልከት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ሰጥቷል።   የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ ሀላፊ አቶ ግዛው ጋግያብ በወቅቱ እንዳሉት በክልሉ የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተለያዩ ኢንሼቲቮች ተቀርፀው እየተተገበሩ ይገኛሉ። በዲጅታል ኢኮኖሚ የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማሳደግም የ5 ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለክልሉ ወጣቶች በመስጠት የዕድሉ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በተያዘው ዓመት በክልሉ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን ለመውሰድ ከተመዘገቡ ከ11ሺህ በላይ ወጣቶች መካከል ከ8 ሺህ 400 በላይ ወጣቶች በአሁኑ ወቅት ስልጠና ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። የግንዛቤ እጥረት፣ በአንዳንድ አካባቢዎች የኢንተርኔት ችግርና ቅንጅታዊ አሰራር አለመጠናከር በዓመቱ ለማሰልጠን በተያዘው ዕቅድ ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ማሳደሩን አመልክተዋል። በቀጣይ አራት ወራት የግንዛቤ ችግሩን በመፍታትና ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከር 50ሺህ ወጣቶችን መዝግቦ ለማሰልጠን በንቅናቄ እንደሚሰራም አስታውቀዋል።   በመድረኩ የተገኘው የክልሉ ብልፅግና ፓርቲ ወጣቶች ክንፍ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ ወጣት ሰይድ ኢብራሂም በበኩሉ እንደገለጸው፣ እንደሀገር የዲጂታል ኢኮኖሚን ለመገንባት እየተደረገ ባለው ጥረት ውስጥ ወጣቱ ግንባር ቀደም ተሰላፊና ተጠቃሚ መሆን አለበት። የተጀመረው የ5 ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናም ለወጣቱ ትልቅ እድል ይዞ በመምጣቱ የወጣት ክንፍ አመራሮች ለስልጠናው መሳካት ሀላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል ብለዋል።   የቦንጋ ከተማ አስተዳደር የብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ ወጣት ታሪኩ አለማየሁ፣ ስልጠናው ያለውን ፋይዳ ለወጣቶች በማስገንዘብ የዕድሉ ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚሰራ ተናግሯል። በመድረኩ ላይ የፌደራል ወጣት ክንፍ አባላት፣ የክልል ሥራ አስፈፃሚ፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር የወጣት ክንፍ አመራሮች ተሳትፈዋል።  
የክህሎት ውድድሩ ዘርፉን መምራት የሚችል የሰው ሃይል ለማፍራት ያግዛል
Apr 29, 2025 63
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦በተማሪዎች መካከል የሚካሔደው የክህሎት ውድድር ዘርፉን መምራት የሚችል ብቃት ያለው የሰው ሃይል ለማፍራት እንደሚያግዝ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ገለፁ። አራተኛው ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር እና 12 ኛው የቱሪዝምና እንግዳ ተቀባይነት ሳምንት ማስጀመርያ መርኃ ግብር እየተከናወነ ይገኛል። በመርኃ ግብሩ ላይ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ፣ የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ነጋሽ እንዲሁም የቱሪዝም ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በየጊዜው የሚካሔደው የክህሎት ውድድር በዘርፉ ብቃት ያለው የሰው ሃይል ለማፍራት ትልቅ አቅምን የሚፈጥር ነው። የክህሎት ውድድሩ የሚሳተፉ ተማሪዎች የተሻለ አቅም ይዘውና ነጥረው እንዲወጡ የሚያግዝ መሆኑንም አንስተዋል። በተጨማሪም ተማሪዎቹ በሀገር አቀፍ እና በአለም አቀፍ ውድድሮች ላይ የመሳተፍ እድል እንዲኖራቸው ያደርጋል ነው ያሉት። ተወዳዳሪዎቹ ሀገራቸውን በመወከል በአለም መድረክ እንዲወዳደሩ የሚያስችል እድል እንደሚያስገኝላቸውም ጠቅሰዋል። የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ነጋሽ በበኩላቸው፤ኢንስቲትዩቱ የቱሪዝም ዘርፉ ክህሎት ባላቸው ዜጎች እንዲመራ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል። አራተኛው ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር እና 12ኛው የቱሪዝምና እንግዳ ተቀባይነት ሳምንት "ብሩህ አእምሮዎች በክህሎት የበቁ ዜጎች" በሚል መሪ ሀሳብ ከዛሬ ሚያዝያ 21 እና 22 ቀን 2017 ዓም ይካሄዳል።
በፈጠራ ስራ ችግር ፈቺ ውጤቶችን በማበርከት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ማሳደግ ተችሏል
Apr 29, 2025 69
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦መንግስት ለአገር ውስጥ ምርት የሰጠው ትኩረት ችግር ፈቺ የፈጠራ ውጤቶችን በማበርከት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እድል ፈጥሯል ሲሉ በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ የፈጠራ ስራ ባለሙያዎችና አምራቾች ገለጹ። መንግስት የአገር ውስጥ ምርትን በማበረታታት ምርትና ምርታማነትን ለማስፋት የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑ ይታወቃል። በተለይም በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአገር ውስጥ ምርቶችን በስፋትም በጥራትም በማምረት ከአገር ውስጥ አልፎ ለውጭ ገበያ የማቅረብ እድል ማመቻቸት ተጠቃሽ ነው። እንዲሁም የስታርት አፖችን አቅም ከማጎልበትና ድጋፍ ከማድረግ ባለፈ የፈጠራ ስራዎች ጥቅም ላይ እንዲውሉ ምቹ እድል መፍጠሩ አይዘነጋም። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የፈጠራ ባለቤቶችና የአገር ውስጥ አምራቾች እንደገለጹት፥ በአሁኑ ወቅት በመንግስት በኩል ዘርፉን ለማገዝ የሚደረጉ ተግባራት የሚበረታቱ ናቸው። የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ መምህራንና ተመራማሪዎች በጋራ በመሆን የሰሩት የእንሰት ምርት ማቀነባበሪያ የፈጠራ ስራ አንዱ ማሳያ ተደርጎ ይወሰዳል። የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ በላይ ጣፋ (ዶ/ር) እንደገለጹት ቴክኖሎጂው እንሰትን በቀላሉ ወደ ምግብነት ለመቀየር የሚያግዝ ነው። ቆጮ በባህላዊ የአዘገጃጀት ዘዴ ሲመረት ከፍተኛ የሰው ጉልበትን የሚጠይቅና የምርት ብክነትን የሚያስከትል ከመሆኑ ባሻገር ለምግብነት ለማዋል ከሶስት እስከ አራት ወር ጊዜ እንደሚወስድ ገልጸዋል። በምርምር የበለጸገው ቴክኖሎጂ ምርቱ በጥራት እንዲመረት ከማድረጉ በተጨማሪ ጊዜውን ወደ ሰባት ቀን ማሳጠር የቻለ ነው። በዚህም ቆጮን ከአገር ውስጥ አልፎ ወደ ውጭ ገበያ ለመላክ አስፈላጊው ሂደት በመጠናቀቁ በቅርቡ ምርቱ ለውጭ ገበያ እንደሚቀርብ አስታውቀዋል። የዳፍ ቴክ ድርጅት መስራችና ባለቤት አቶ ደነቀው በሪሁን ድርጅታቸው የተለያዩ የፈጠራ ስራዎችንና ቴክኖሎጂዎችን እያመረተ እንደሚገኝ አንስተዋል። የውሃና የመብራት ቆጣሪን ዲጂታላይዝ ለማድረግ የተሰራው የፈጠራ ስራ ዘርፉን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ለመምራትና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያግዝ ነው ብለዋል። ቴክኖሎጂው በሙከራ ደረጃ ተግባራዊ በተደረገባቸው የመንግስት ተቋማት ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱ በመታመኑ በአእምሯዊ ንብረት መመዝገቡን ጠቁመዋል፡፡ የየትም ትሬዲንግ ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ኢክራም አኪል እንደገለጹት፥ ድርጅታቸው ከውጭ ይገቡ የነበሩ የውበት መጠበቂያ ምርቶችን በአገር ውስጥ የመተካት ስራን እያከናወነ ይገኛል። በድርጅቱ የሚመረቱ ምርቶች በጥራትም በአይነትም ሰፊ መሆናቸውን ጠቁመው በሚፈጠር የገበያ ትስስርና የአቅርቦት ሰንሰለት ምርቱን ተደራሽ እያደረገ ይገኛል ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ የስታርት አፕ እና የቴክኖሎጂ ፈጠራ ማዕከል እየሆነች ነው - ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)
Apr 29, 2025 96
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በመንግስት እና የግሉ ዘርፍ ትብብር የስታርት አፕ እና የቴክኖሎጂ ፈጠራ ማዕከል እየሆነች ነው ሲሉ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ። "ኢኖቬሽን አፍሪካ 2025" የአፍሪካ የትምህርት፣ አይ ሲ ቲ እና ክህሎት የሚኒስትሮች ስብሰባ "በ21ኛው ክፍለ ዘመን አፍሪካን ማስተማርና ማብቃት" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው።   የትምህርት ሚኒስቴር፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአፍሪካን ብሬይን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት አህጉራዊ ጉባኤ ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል። የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ በሪፎርም፣ አቅም ግንባታ፣ የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ሽግግር እንዲሁም ስትራቴጂካዊ ትብብር በመፍጠር የአፍሪካን መፃኢ ጊዜ ለመወሰን ያለመ ነው። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) "ለኢኖቬሽን እና ትምህርት ሽግግር የዲጂታል ቴክኖሎጂን አቅም መገንባት" በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄደውን የፓናል ውይይት አስጀምረዋል። ሚኒስትሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ የበለጸገችና በቴክኖሎጂ ያደገች ሀገር ለመገንባት ወሳኝ ሁነት ነው። በአፍሪካ የዲጂታል ክህሎት እና የቴክኖሎጂ ፈጠራ አቅምን በማሳለጥ ልማትና እድገትን ማቀላጠፍ ያስችላል ብለዋል። ወጣቶችን የዲጂታል ቴክኖሎጂ ማስታጠቅ ምርጫ ሳይሆን ግዴታ መሆኑን ተናግረዋል። የአፍሪካ ወጣቶች ዓለም አቀፍ ተሳትፎ የሚወሰነው በሚኖራቸው የቴክኖሎጂ አቅም መሆኑንም ጠቅሰዋል። በመሆኑም ሁሉን አቀፍ ፖሊሲ በመተግበር የዲጂታል ውጤታማነት እና ምርታማነትን ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል። በአፍሪካ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ የዲጂታል ኢኮኖሚ ለመገንባት የጋራ ጥረትን እንደሚጠይቅ ተናግረዋል። ለዚህ ደግሞ ኢትዮጵያ በትብብር በመስራት ሁሉንም የፈጠራ አቅሞች በመጠቀም ለወጣቶች ምቹ የዲጂታል ስነ ምህዳር ለመፍጠር ቁርጠኛ መሆኗን ገልጸዋል። አፍሪካን በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ወጣቶችን በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ኢንጂነሪንግ እና ሒሳብ ትምህርቶች ማብቃት እንደሚያስፈልግም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ኢንጂነሪንግ እና ሒሳብ ትምህርቶች ለእድገት ወሳኝ መሆናቸውን በመገንዘብ ያልተቋረጠ ጥረት እያደረገች መሆኑንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በመንግስትና የግሉ ዘርፍ የጋራ ጥረት የስታርት አፕ እና የቴክኖሎጂ ፈጠራ ማዕከል እየሆነች ነው ያሉት ሚኒስትሩ፣ በኢንዱስትሪዎች እና ትምህርት ተቋማት መካከል ትብብርን በማዳበር ለስራ ፈጣሪዎች ምቹ ከባቢ እንዲኖር እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል። ለችግሮቻችን መፍትሔ ለማበጀት ሁሉንም የኢኖቬሽን አቅም መጠቀም እንደሚገባ ገልጸው፣ ኢትዮጵያ ስታርት አፕን ለማሳደግ የፖሊሲ ዝግጅት እያደረገች መሆኑንም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ የአጋርነት ትብብሯን እያጠናከረች ነው
Apr 28, 2025 84
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 20/2017 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ከአጋሮች ጋር ያላትን የጋራ ትብብር በማጠናከር ላይ እንደምትገኝ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን አለማየሁ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከፈረንሳይ እና ከሱዳን ምሁራን ጋር የዲጂታል ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ስርዓትን ለማጎልበት የሚያስችል አውደ ጥናት እያካሄደ ነው።   ከኢትዮጵያ፣ ከፈረንሳይ እና ከሱዳን የትምህርት ተቋማት የተውጣጡ ምሁራን፣ ተመራማሪዎች እና ከፍተኛ ባለሙያዎች በአውደ ጥናቱ ላይ ተሳትፈዋል። አውደ ጥናቱ በኢትዮጵያ፣ በፈረንሳይ እና በሱዳን ምሁራኖች መካከል በትምህርት፣ በኢኖቬሽን፣ በቴክኖሎጂ፣ በዲጂታል እውቀት እና ዲጂታል ኢኮኖሚ ላይ በጋራ መስራትን ታሳቢ ያደረገ እንደሆነ ተገልጿል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን አለማየሁ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ዲጂታል ኢኮኖሚን ለመገንባት በሚያስችሉ የትምህርት ጉዳዮች ዘርፍ ላይ ከአፍሪካ እና ከሌሎች አጋር ዓለም ሀገራት ጋር በትብብር እየሰራች ነው ብለዋል። የዲጂታል ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ለማጎልበት የሚካሄደው አውደ ጥናት ለሀገራቱ ጉልህ አበርክቶ እንዳለው ገልጸዋል። በሱዳን የፈረንሳይ አምሳደር እና የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ በርትራንድ ኮቼሪ በሀገራቱ ዘመኑ የሚሻውን ቴክኖሎጂ ለማስታጠቅ፣ ወጣቶች የአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ክህሎት እና እውቀት ባለቤት እንዲሆኑ የሚያስችሉ ፕሮጀክቶችን መተግበር እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል። በሱዳን የኢትዮጵያ አምባሳደር ኤል ዛይን ኢብራሂም ሁሴን አውደ ጥናቱ በሀገራቱ መካከል ያለውን የትብብር ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ ከፍተኛ ጠቃሜታ አለው ብለዋል። አውደ ጥናቱ ለሶስት ቀናት እንደሚቆይ የሚኒስቴሩ መረጃ ያመለክታል።
የአእምሯዊ ንብረት ጥበቃና ምዝገባን ከሰባት ሺህ በላይ ለማሳደግ እየተሰራ ነው -የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን
Apr 28, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 20/2017(ኢዜአ)፦የአእምሯዊ ንብረት ጥበቃና ምዝገባን በዘንድሮው ዓመት ወደ ሰባት ሺህ 5 መቶ ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን አስታወቀ። በኢትዮጵያ ለ23ኛ ግዜ የሚከበረው የዓለም አቀፍ የአእምሯዊ ንብረት ቀን በተለያዩ መርሀ ግብሮች መከበር ጀምሯል።   እለቱን አስመልክቶ የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ወልዱ ይመስል እንደገለፁት የፈጠራ ስራ ውጤቶች ለአገር ገፅታ ግንባታ፣ ለስራ እድል ፈጠራና ለቴክኖሎጂ መስፋፋት ጉልህ አስተዋጽኦ አላቸው። ከፈጠራ ስራ ዘርፎች መካከል የሙዚቃ ፈጠራ ስራ በሁሉም መስክ ለሚከናወኑ ተግባራት አጋዥ መሳሪያ ስለመሆኑም አንስተዋል። ኢትዮጵያ ብዙ ባህል፣ እሴትና ትውፊት ያላት አገር መሆኗ ደግሞ ለሙዚቃ ፈጠራ ስራ መጎልበት ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር ነው። መንግስት የሙዚቃና መሠል የፈጠራ ስራዎች እንዲጠበቁና ለአገር ያላቸውን ፋይዳ ይበልጥ እንዲያጎሉ የሚያስችሉ የአሰራር ስርዓቶች እየዘረጋ መሆኑንም አብራርተዋል። በዚህ ረገድ ባለስልጣኑ የአገራትን ተሞክሮ በመቀመር፣ ከዘርፉ ተዋንያን ጋር ያለውን ቅንጅታዊ አሰራር በማጠናከርና የምዝገባና መሰል አሰራሮችን በቴክኖሎጂ የተደገፈ ማድረግ ከተከናወኑ ተግባራት መካከል ተጠቃሽ ናቸው። ዋና ዳይሬክተር እንደገለጹት የፈጠራ ስራን ከማበረታታ በዘለለ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታውን ለማጉላት ምቹ እድልን እየፈጠረ ይገኛል። ለአብነትም ባለፈው አንድ አመት ብቻ ከ5 ሺህ በላይ የምዝገባና የጥበቃ ስራ ማከናወን ማቻሉን ገልጸው በዘንድሮው አመትም ወደ 7 ሺህ 5 መቶ ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ዘርፉን ይበልጥ ለማዘመን፣ ተደራሽነቱን ለማስፋትና የፈጠራ ሰራ ባለሙያዎች ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ምቹ ሁኔታን እየፈጠረ መሆኑን አክለዋል።   የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) በበኩላቸው የቴክኖሎጂ እድገትን ለማረጋገጥ የፈጠራ ስራ ትልቁን ድርሻ እንደሚወስድ ተናግረዋል። የአእምሯዊ ንብረት መብት እና የቅጅ መብት ስራዎችን ለማስጠበቅ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው ህጋዊ አሰራር በተቀናጀ መልኩ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። በዚህ ረገድ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችና የፈጠራ ስራዎች ለአገር ልማትና ለዜጎች አብሮነት የድርሻቸውን እንዲወጡ በማድረግ ረገድ በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግ ገልጸው፤ የመብት ማስጠበቅ ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል። የፈጠራ ስራ ውጤቶችን በአግባቡ ጥቅም ላይ በማዋል ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታውን ለማጉላት በትኩረት እየተሰራ ስለመሆኑም ሚኒስትር ዴኤታው አብራርተዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የፈጠራ ውጤቶች አውደርዕይ የተከፈተ ሲሆን የበዓሉ ተሳታፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች አውደ ርዕዩን ጎብኝተውታል። የዘንድሮው አለም አቀፍ የአእምሯዊ ንብረት ቀን "ሙዚቃና አእምሯዊ ንብረት ፤ ፈጠራን ማጎልበት/ ማፍጠን'' በሚል መሪ ሀሳብ ከዛሬ ጀምሮ ለሁለት ቀናት በተለያዩ ሁነቶች የሚከበር መሆኑም ተገልጿል።    
በአማራ ክልል የፈጠራ ሥራዎችን በማበረታታት እድገትን ለማፋጠን የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Apr 28, 2025 76
ደሴ ፤ ሚያዚያ 20/2017(ኢዜአ)፡ -በአማራ ክልል የቴክኖሎጂና የፈጠራ ሥራዎችን በመደገፍና በማበረታታት እድገትን ለማፋጠን የሚያስችሉ ተግባራት በቅንጅት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን(ዶ/ር) ገለጹ። የአማራ ብረታብረት ኢንዱስትሪና ማሽን ቴክኖሎጂ ልማት ኢንተርፕራይዝ የሰራቸውን ማሽኖች የርክክብ ሥነ- ሥርዓት ዛሬ በኮምቦልቻ ከተማ ተካሂዷል።   ከክልሉ ስራና ስልጠና ቢሮ ጋር በተከናወነው የርክክብ ሥነ-ሥርዓት ላይ የተገኙት የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን(ዶ/ር) እንደተናገሩት ፤ በክልሉ የብልጽግና ጉዞን ለማሳካት ትኩረት ተሰጥቷል። በተለይ ተቋማት አሰራራቸውን በቴክኖሎጂ በማዘመን ተገልጋዩ ህብረተሰብ የተሻለ ተጠቃሚ እንዲሆን ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ለፈጠራና ለቴክኖሎጂ ስራዎች ደግሞ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ በማበረታታት የወጣቶችን እውቀትና ክህሎት ማሳደግ ላይ እየተሰራ ነው ብለዋል። የክልሉ የልማት ድርጅቶች አካል የሆነው የአማራ ብረታብረት ኢንዱስትሪና ማሽን ቴክኖሎጂ ልማት ኢንተርፕራይዝን በመደገፍና የገበያ ትስስር በመፍጠር ሥራውን እንዲያዘምንም እንዲሁ።   የኢንተርፕራይዙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ዘላለም በላይ በበኩላቸው፤ ኢንተርፕራይዙ የኢንዱስትሪና የግብርና መገልገያ ማሽኖችን በማምረት ለተጠቃሚዎች እያቀረበ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በቴክኖሎጂ የታገዙ ማሽኖችን በመፍጠር፣ በማላመድና በማስፋት ላይ በማተኮር የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በኢንተርፕራይዙ የተሰሩ 117 የእንጨት መሰንጠቂያ፣ የበቆሎ መፈልፈያ፣ ሞተርና ሌሎችንም ማሽኖችን አሻሽሎ በመስራት ዛሬ ለክልሉ ሥራና ስልጠና ቢሮ ማስረከባቸውን አስታውቀዋል። ማሽኖቹ ተግባር ተኮር ሥልጠናን የሚያጠናክሩ፣ የኢንዱስትሪና የግብርና ሥራዎችን የሚያዘምኑ በመሆናቸው ተፈላጊ ናቸው ያሉት ደግሞ የአማራ ክልል ስራና ስልጠና ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ስቡህ ገበያው ናቸው።   የተረከቧቸውን ማሽኖች ለተለያዩ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች በማከፋፈል ፈጥነው ጥቅም ላይ እንዲውሉ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የአማራ ክልል ገንዘብ ቢሮ ኃላፊና የኢንተርፕራይዙ የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ጥላሁን መሀሪ፤ ኢንተርፕራይዙ ዘመኑን የዋጀ የተሻለ አሰራር እንዲኖረው ድጋፍ እየተደረገ ነው ሲሉ ገልጸዋል። በርክክብ ሥነ ሥርዓቱ ፤ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራር አባላትና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።    
በክልሉ የፈጠራና የቴክኖሎጂ ውጤቶች ፈጥነው ህብረተሰቡ ጋር እንዲደርሱ ባለድርሻ አካላት ሚናቸውን ማጠናከር አለባቸው - አፈ ጉባኤ ሰዓዳ አብዱራህማን
Apr 28, 2025 79
አዳማ፤ ሚያዝያ 20/2017(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የፈጠራና የቴክኖሎጂ ውጤቶች ፈጥነው ህብረተሰቡ ጋር እንዲደርሱ ባለድርሻ አካላት ሚናቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ሰዓዳ አብዱራህማን ገለጹ። 6ኛው ዙር የኦሮሚያ የፈጠራ፤ ቴክኖሎጂና የንግድ ስራ ክህሎት ውድድርና አውደ ርዕይ በጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ሰዓዳ አብዱረህማንና በምክትል ፕሬዚዳንት ማዕረግ የኦሮሚያ ከተሞች ክላስተር አስተባባሪ አቶ መስፍን መላኩ ተከፍቷል። በወቅቱ አፈ ጉባኤዋ እንደገለፁት ወጣቶች ቴክኖሎጂን በማላመድ የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች መፍታት የሚያስችሉ የፈጠራ ውጤቶች ማውጣት አለባቸው። በተለይ የፈጠራና የቴክኖሎጂ ግኝቶችና ውጤቶች ፈጥነው ህብረተሰቡ ዘንድ በስፋትና በተሻለ ጥራት እንዲደርሱ ማድረግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ሰርቶ የመለወጥ እሳቤ እንዲጎለብት፤ በክህሎትና በቴክኖሎጂ ፈጠራ የበቁ ወጣቶችን ከማፍራት አኳያ በተሻለ ፍጥነት መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል። የፈጠራና የቴክኖሎጂ ውጤቶች በልፅገው ወደ ልማቱ እንዲገቡ የክልሉ መንግሥት በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል። በምክትል ፕሬዘዳንት ማዕረግ የኦሮሚያ ክልል ከተሞች ክላስተር አስተባባሪ አቶ መስፍን መላኩ በበኩላቸው በተቋማቱና በፈጠራ ባለቤቶች የወጡ ቴክኖሎጂዎች የህዝቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች እየፈቱ መሆናቸው ተናግረዋል። በተለይ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጆች በክህሎትና በስራ ፈጠራ ላይ እየሰሩ ያሉት የፈጠራና ቴክኖሎጂ ልማት ስራዎች የብልፅግናን ጉዞ ለማሳካት መሰረት የሚጥል ነው ብለዋል። የማኑፋክቸሪንግና የጎጆ ኢንዱስትሪን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማሻገር 'ሲንቄ ሊዝ ማሽን ኢንሼቲቭ' የተሰኘ መጀመሩን ጠቅሰው ይህም የፈጠራና ቴክኖሎጂ ውጤቶችን በማበልፀግ ከውጭ የሚገቡ ማሽኖችን መተካት አስችሏል ብለዋል። በፈጠራ የወጡ ቴክኖሎጂዎች ውጤቶች ለምተው በስፋት ለአርሶ አደሩና ለከተማው ህብረተሰብ እንዲቀርቡ የክልሉ መንግሥት ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል። ቴክኖሎጂን በመቅዳትና በማላመድ የክልሉ ኮሌጆች በተሻለ ደረጃ እየተንቀሳቀሱ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የኦሮሚያ ክልል የስራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ ሃላፊ አቶ ኤባ ገርባ ናቸው። ወጣቶች ሰፊ የስራ ዕድል መፍጠር የሚችል የኢንተርፕርነርሽፕ፤ የክህሎትና የንግድ ስራ ፈጠራ ላይ በስፋት እንዲሳተፉ በአቅም ግንባታና በሰርቶ ማሳያ ጭምር ከፖሊ ቴክኒክ ኮሌጆች ጋር በቅርበት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በውድድሩና አውደ ርዕዩ በ21 የውድድር አይነቶች በክህሎት፤ በቴክኖሎጂ፤ በንግድ ስራ ፈጠራና በቴክኖሎጂ ምርምር 400 የሚሆኑ ተወዳዳሪዎች ተሳታፊ እንደሚሆኑ ገልጸዋል።
በፈጠራ ሥራችን ሀገራዊ ልማትን ለሚያግዙና ከውጭ የሚገቡትን ለሚተኩ ምርቶች ትኩረት ሰጥተናል - የፈጠራ ባለቤቶች
Apr 28, 2025 67
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 20/2017(ኢዜአ)፦ በፈጠራ ሥራቸው ሀገራዊ ልማትን ለሚያግዙና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን ለመተካት ትኩረት መስጠታቸውን በሲዳማ ክልል የፈጠራ ባለቤቶች ገለጹ። የሲዳማ ክልል ሥራ፣ ክህሎትና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ በበኩሉ የቴክኖሎጂ ፈጣሪዎችን ለማበረታታትና ምርቶቻቸውን ተደራሽ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ገልጿል። የክልሉ የቴክኖሎጂ ክህሎትና የጥናትና ምርምር አውደ ርዕይና ውድድር "ብሩህ አዕምሮዎች የተፍታቱ እጆች በክህሎት የበቁ ዜጎች" በሚል መሪ ሀሳብ ተካሂዷል። በውድድሩ የፈጠራ ሥራቸውን ይዘው ከቀረቡት መካከል የሀዌላ ቱላ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ መምህር ሀብታሙ ዘካሪያስ በአንድ ጊዜ አራት ሰዎችን የሚያጓጉዝ ብስከሌት ይዞ መቅረቡን ተናግሯል። የፈጠራ ስራው በሀዋሳ ከተማ በአሁኑ ወቅት እየተከናወነ ያለውን የኮሪደርና አረንጓዴ ልማት ታሳቢ ማድረጉን ጠቁሞ፣ ሳይክሉን በአንድ ጊዜ አራት ሰዎች የሚያሽከረክሩት መሆኑን ገልጿል። ምርቱ ከውጭ ይገባ የነበረውን ሳይክል የሚተካና በተሻለ ዋጋ መቅረቡን ገልጾ፣ በአንድ ጊዜ አራት ሰዎችን ማሳፈሩ በኮሪደር መንገድ ላይ ሰዎች እየተዝናኑ መጓጓዝ ያስችላቸዋል ብለዋል። ከሀዋሳ ተግባረ ዕድ ቴክኒክ ኮሌጅ መምህር ተካልኝ ተሻለ በበኩላቸው አነስተኛ የክብደት ማንሻ ወይም የክሬን ተሽከርካሪ መስራታቸውን ገልጸዋል። የፈጠራ ሥራውን በሀዋሳ ከተማ ከጽዳት ሥራ ጋር በተያያዘ ያለውን ችግር መነሻ በማድረግ መስራታቸውንም ነው የተናገሩት። በቀላል የኤሌክትሪክ ሃይል የእህል መፍጫ ማሽን የሰራው ደግሞ በሀዋሳ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የደረጃ 3 ተማሪ ይስማ ዎያሞ፣ የፈጠራ ውጤቱ በገጠር በሴቶች ላይ በድንጋይ ወፍጮ ሲደርስባቸው የነበረውን ጫና የሚያቃልል መሆኑን ተናግሯል። የሲዳማ ክልል ሥራ ክህሎትና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ፍስሃ ፍቾላ በቴክኖሎጂ ፈጠራ የተሰማሩትን የመደገፍና የማብቃት ስራ እየተሰራ መሆኑ ገልጸዋል። የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆችን የክህሎት ማፍለቂያ ለማድረግ አበረታች ሥራዎች እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። ውድድሩ በአሰልጣኝ፣ ሰልጣኝና ኢንተርፕራይዞች መካከል የተደረገ መሆኑን ጠቅሰው፣ የቴክኖሎጂ ፈጣሪዎች ልምድ የሚለዋወጡበትና የገበያ ትስስር የሚፈጥሩበት መሆኑንም አስረድተዋል። ከሁሉ በላይ ቴክኖሎጂዎች ተደራሽ እንዲሆኑና የቴክኖሎጂ ፈጣሪዎችን የገበያ ትስስር ችግር ለመፍታት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ኮሌጆች ያመረቱትን በራሳቸው በመሸጥ የውስጥ ገቢያቸውን እንዲያሳድጉ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፣ ይህም ኮሌጆቹ በፋንይናንስ አቅርቦት የሚያጋጥማቸውን እጥረት ለመፍታት እያስቻላቸው መሆኑን ገልጸዋል።
በአፍሪካ የወጣቶችን ክህሎትና የፈጠራ አቅም ለማሳደግ የተግባር ትብብርና ቁርጠኝነት ያስፈልጋል - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 28, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2017(ኢዜአ)፦ በአፍሪካ የወጣቶችን ክህሎትና ፈጠራ አቅም ለማሳደግ ከንግግር ያለፈ የተግባር ትብብርና ቁርጠኝነት እንደሚያስፈልግ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። "ኢኖቬሽን አፍሪካ 2025" የአፍሪካ የትምህርት፣ አይ ሲ ቲ እና ክህሎት የሚኒስትሮች ስብሰባ "በ21ኛው ክፍለ ዘመን አፍሪካን ማስተማርና ማብቃት" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው። የትምህርት ሚኒስቴር፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአፍሪካ ብሬይን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት አህጉራዊ ጉባኤ ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት ይቆያል።   ጉባኤው የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ በሪፎርም፣ አቅም ግንባታ የቴክኖሎጂ ስትራቴጂካዊ ትብብር በመፍጠር የአፍሪካን የትምህርት ተደራሽነት ማስፋት ያለመ ነው። በመርሀ ግብሩ ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የትምህርት ሚኒስትር፣ ብርሀኑ ነጋ(ፕ/ር)፣ የተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት የትምህርት ሚኒስትሮች፣ አምባሳደሮች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የሰው ልጅ መገኛ የሆነችው ኢትዮጵያ የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ በማዘጋጀቷ ክብር ይሰማታል። ጉባኤውም የትምህርት ጥራት፣ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ልህቀት አፍሪካን የሚያነቃቃ እና የወጣቱን የወደፊት እጣ ፋንታ የሚወስን መሆኑን ገልጸዋል።   ለአንድ ሀገር እድገት ትምህርት ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፤ ለዚህ ደግሞ የመምህራንን ክብር መጠበቅ፣ ማነቃቃትና አቅማቸውን ማጎልበት፣ የተማሪዎችን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ማሳደግ ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ ለትምህርት፣ ለክህሎት ማሳደግና ፈጠራ ቅድሚያ ትሰጣለች ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አዳዲስ ትምህርት ቤቶችን ለመገንባት፣ መሰረተ ልማት ለማስፋፋት፣ ፈጠራን ለማዳበር ከፍተኛ ገንዘብ ፈሰስ እያደረገች መሆኑን ገልጸዋል። የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ ከኢትዮጵያ ራዕይ ጋር የተጣጣመ መሆኑን ጠቅሰው፣ በጉባኤው ከንግግር ያለፈ ግልጽ እና ትርጉም ያለው ትብብር ገቢራዊ ማድረግ ይገባል ብለዋል። ዓለም የተለያዩ ችግሮች የሚስተዋሉባት በመሆኗ ከዚህ ችግር ለመውጣት በአፍሪካ ያለውን ተስፋ በትብብር መጠቀም ይገባል ነው ያሉት። ትምህርት ቁሳቁስ ብቻ ሳይሆን ሰብዓዊ ክብር ጭምር ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የአፍሪካ ወጣቶች ትልልቅ ስራዎችን እያለሙ በመሆኑ ልጆቻችን ህልማቸውን እንዲያሳኩ በህብረትና በፍጥነት መስራት ይገባናል ብለዋል። በአፍሪካ ተሰጥኦ ያላቸው ወጣቶችን ለማሳደግ አቅማቸውን እንዲጠቀሙ ልንመራቸውና ልናነሳሳቸው ይገባል ነው ያሉት።   የትምህርት ሚኒስትር ብርሀኑ ነጋ(ፕ/ር)፣ በአፍሪካ ብሎም በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው ነባራዊ ሁኔታ ጥንቃቄ እና አስተውሎት የሚጠይቅ መሆኑን ገልጸዋል። የአፍሪካን የወደፊት እጣ ፋንታ ለመወሰን ወጣቶችን በክህሎት ማብቃትና በፈጠራ ማላቅ ይገባል ብለዋል። በአፍሪካ በክህሎት፣ በቴክኖሎጂ እና ፈጠራ ዘርፍ አዲስ ታሪክ ለመፃፍ በስፋት መነጋገርና መዘጋጀት አለብን ሲሉም ገልጸዋል።
በክልሉ ወጣቶች ራሳቸውን በቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት እንዲያበለጽጉ የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ ይቀጥላል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Apr 27, 2025 105
ደሴ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ወጣቶች ራሳቸውን በቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት እንዲያበለጽጉ የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። 9ኛው የክልሉ የቴክኖሎጂ፣ የክህሎት፣ የተግባራዊ ጥናትና ምርምር እና የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች የንግድ ትርዒት እና የደረጃ ሽግግር ሳምንት በኮምቦልቻ ከተማ ተከፍቷል። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት ለወጣቶች ልዩ ትኩረት በመስጠት በቴክኖሎጂ፣ በስልጠናና በክህሎት ዳብረው ሥራ ፈጣሪ መሆን እንዲችሉ ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የሀገር ውስጥ ባለሃብቶችን በማበረታታት የክልሉን ኢኮኖሚ የበለጠ ለማነቃቃት እንደሚሰራ ጠቁመው፤ በጥቃቅንና አነስተኛ ዘርፍ የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች ወደ ባለሃብትነት ሲሸጋገሩም አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ተናግረዋል። በተለይም ወጣቶች ራሳቸውን በቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት እንዲያበለጽጉ የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት።   በመርሃ ግብሩ የተገኙት የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፋሪሃት ካሚል በበኩላቸው በቴክኖሎጂ የበለጸገ ትውልድ በመፍጠር ለዜጎች የተሻለ የሥራ እድል ለማመቻቸት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በተለይም የወጣቶችን የፈጠራ ሥራ በማበረታታትና በማጎልበት በኢኮኖሚ እራሳቸውን ከመቻል ባለፈ ለሀገርና ለዓለም መትረፍ እንዲችሉ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ወጣቶች በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ተሰማርተው በመስራት ከአነስተኛ ወደ ባለሃብትነት እንዲሸጋገሩ ለማድረግም የማሰልጠን፣ የመስሪያና የመሸጫ ቦታ የማመቻቸት ተግባራት ይከናወናሉ ብለዋል። ዛሬ በአማራ ክልል የተመለከትነው የፈጠራ ሥራ፣ የቴክኖሎጂ ውጤትና የወጣቶች ተነሳሽነት የሚበረታታና የሚደነቅ በመሆኑ የበለጠ ማደግ እንዲችል ተገቢው ድጋፍ ይደረጋል ነው ያሉት። የአማራ ክልል ስራና ስልጠና ቢሮ ኃላፊ ስቡህ ገበያው(ዶ/ር) በበኩላቸው ወጣቶችን በቴክኖሎጂ በማገዝ ክህሎታቸውን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ከዛሬ ጀምሮ ለአምስት ቀናት በሚቆየው የንግድ ትርኢትና የደረጃ ሽግግር ሳምንት በቴክኖሎጂው ዘርፍ 345 አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ወደ ታዳጊና መካከለኛ ባለሀብትነት የሽግግር መርሃግብር መኖሩን ተናግረዋል። በፕሮግራሙ የክልሉ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ፋንቱ ተስፋዬ፣ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን(ዶ/ር) እና በምክትል ርእሰ መሥተዳደር ማዕረግ የከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ እና የከተሞች እና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አህመዲን መሀመድ(ዶ/ር) እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል።
የአማራ ክልል የቴክኖሎጂ፣ የክህሎት እና የተግባራዊ ጥናትና ምርምር የንግድ ትርኢት ሳምንት በኮምቦልቻ ከተማ ተከፈተ
Apr 27, 2025 81
ደሴ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ የአማራ ክልል 9ኛው የቴክኖሎጂ፣ የክህሎት፣ የተግባራዊ ጥናትና ምርምር እና የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች የንግድ ትርዒት እና የደረጃ ሽግግር ሳምንት በኮምቦልቻ ከተማ ተከፈተ። የንግድ ትርኢትና የደረጃ ሽግግር ሳምንቱን የከፈቱት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ እና የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፋሪሃት ካሚል ናቸው። በሥነ-ስርአቱ የአማራ ክልል ሥራና ስልጠና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ አማረ አለሙ እንደገለፁት ፕሮግራሙ በዘርፉ የተሰማሩ ሙያተኞች የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን ማዳበር የሚያስችል ነው።   ከዛሬ ጀምሮ ለአምስት ቀናት በሚቆየው የንግድ ትርኢትና የደረጃ ሽግግር ሳምንት 110 በክህሎት፣ 75 የቴክኖሎጂ ተወዳዳሪዎች የሚሳተፉ ሲሆን 57 የፈጠራ ሥራዎችም ለእይታ ይቀርባሉ ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በየተሰማሩበት የሥራ ዘርፎች ለውጥ ያመጡ 345 አነስተኛ ኢንተርፕራይዞችም ወደ ታዳጊና መካከለኛ ባለሀብትነት ይሸጋገራሉ ብለዋል። በፕሮግራሙ ላይ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን(ዶ/ር)፣ አፈ-ጉባኤ ፋንቱ ተስፋዬ፣በምክትል ርእሰ መሥተዳደር ማዕረግ የከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ እና የከተሞች እና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር) እና ሌሎች የክልሉ አመራሮች ተገኝተዋል።    
በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ዜጎቻችን ላይ ምሬት የሚፈጥሩ አሰራሮችን ፈትሾ ማስተካከል ቅድሚያ የምንሰጠው ጉዳይ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Apr 26, 2025 197
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 14/2017(ኢዜአ)፦ በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ዜጎቻችን ላይ ምሬት የሚፈጥሩ አሰራሮችን ፈትሾ ማስተካከል ቅድሚያ የምንሰጠው ጉዳይ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ለዚህ ቁርጠኝነታቸን አንዱ ማሳያ የሆነውን የመሶብ የአንድ መስኮት አገልግሎት ማዕከልን ዛሬ መርቀናል ብለዋል።   ይኽን አዲስ ማዕከል የሚገልጡ ሶስት ቁልፍ አላባውያን አሉ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የቆየ እና የተጎዳ ህንፃን ወደ ዘመናዊ እና ሥነውበታዊ ደረጃው ለሥራ ከባቢ አስደሳች ወደ ሆነ ህንፃ መለወጡ አንዱ ነው ሲሉ ገልጸዋል። አገልግሎቶችን ለመሰተር እና ለማቀናጀት በሀገር ውስጥ የለማ ሶፍትዌር በሥራ ላይ መዋሉ ብሎም በታደሰ አመለካከት ብቁ እና ክብር የሞላበት አገልግሎት የሚሰጡ ወጣቶች መዘጋጀታቸው ሌሎቹ አላባውያን ናቸው ብለዋል። 12 ተቋማት በአንድ ጣሪያ ሥር 40 የተለያዩ አገልግሎቶችን መስጠት የጀመሩ ሲሆን ይኽም ዜጎች ጊዜያቸውን እንዲቆጥቡ እና አገልግሎቶችን በተሻለ ውጤታማ መንገድ ለማግኘት ያግዛል ነው ያሉት።   እንደዚህ ያሉ ሥርዓቶችን ማበልፀግ ለዜጎች የተለያዩ የአገልግሎት ርካታ መታጣቶች ምላሽ በመስጠት በሂደት ለሰፊው ማኅበረሰብ ርካታ ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖራቸዋል ሲሉም አክለዋል። የዛሬው ምረቃ ትልቅ ርምጃ መራመዳችንን ያሳያል፤ ኢትዮጵያ በዚህ ማዕከል ላይ ጨምራ እና አስፋፍታ ለዜጎች ሁሉ የተሻለ የአገልግሎት አሰጣጥን ታረጋግጣለች ብለዋል።
መሶብ የአንድ መስኮት አገልግሎት በአንድ ጣራ ስር የተለያዩ የመንግስት አገልግሎቶችን መስጠት ጀመረ
Apr 26, 2025 117
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2017(ኢዜአ)፦ መሶብ የአንድ መስኮት አገልግሎት በአንድ ጣራ ስር የተለያዩ የመንግስት አገልግሎቶችን መስጠት ጀምሯል። መሶብ የአንድ መስኮት አገልግሎት በአንድ ጣራ ስር የተለያዩ የመንግስት አገልግሎቶችን በማጣመር ምርጥ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የሚሰጥ አገልግሎት ነው። የአሰራር ስረዓቱ ዜጎች የተሟላ የዲጂታል አማራጮችን በመጠቀም በቀላሉ የተለያዩ የፌደራል ተቋማትን አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። ይህም ባለጉዳዮች ወደ ተለያዩ ቢሮዎች የሚያደርጉትን ምልልስ፣ረጅም የወረፋ ጥበቃ እና ከወረቀት ጋር ተዛማጅ የሆኑ ስራዎችን የሚያሰቀር ነውም ብሏል፡፡   አሁን ሥራ ለጀመረው የሙከራ ፕሮጀክት አስራ ሁለት የፌደራል መንግስት ተቋማት የተቀላቀሉ ሲሆን አርባ አንድ የሚሆኑ የህዝብ አገልግሎቶችንም ማቅረባቸውንም ገልጿል፡፡ አገልግሎቶቹም ከፈቃድ አሰጣጥ ጀምሮ ፋይዳ ድጅታል የመታወቂያ ምዝገባ እና ሌሎችንም ያካተተ መሆኑን ጽህፈት ቤቱ አስታውቋል።   በአጠቃላይ በፓይለት ፕሮግራም በአንድ ስፍራ የ12 ተቋማት 41 አገልግሎቶች በመሰጠት ላይ የሚገኙ ሲሆን ተቋማቱም፦ 1. የብሄራዊ መታወቂያ አገልግሎት 2. የኢሚግሬሽን እና የዜግነት አገልግሎት 3. የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት 4. የገቢዎች ሚኒስቴር 5. የንግድ እና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር 6. የስራ እና ክህሎት ሚኒስቴር 7. የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን 8. የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር 9. የትምህርት ምዘና እና ፈተናዎች አገልግሎት 10. የኢትዮ ፖስታ 11. የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 12. ኢትዮ ቴሌኮም ሀሉም ተቋማት በቴክኖሎጂ አማካኝነት በትስስር አገልግሎት እየሰጡም ይገኛሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም