ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲና ፋሪስ ቴክኖሎጂ ግሩፕ በጋራ ለመስራት ተስማሙ
Mar 19, 2024 61
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 10/2016(ኢዜአ)፦ አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲና ፋሪስ ቴክኖሎጂ ግሩፕ በምርምርና በፈጠራ ስራ በጋራ ለመስራት የሚያስችል ስምምነት ተፈራርመዋል ። ስምምነቱን የዩኒቨርስቲው ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) የፋሪስ ቴክኖሎጂ ግሩፕ መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ ኤልያስ ይርዳው ተፈራርመዋል። ዶክተር ሳሙኤል በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ዩኒቨርስቲው የአምስት ዓመቱን ስትራቴጂ ለማሳካት ከተያዙ ግቦች መካከል አገራዊ ፋይዳ ካላቸው የግል ዘርፎች ጋር በትብብር መስራት አንዱ ነው ብለዋል። ከፋሪስ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ጋር የተደረገው ስምምነት የስትራቴጂው አካል መሆኑን ጠቅሰው፤ በጥናትና ምርምር እንዲሁም ፈጠራ ላይ በትብብር ይሰራል ብለዋል። ተጠባባቂ ፕሬዝዳንቱ እንዳሉት የተማሪዎች የፈጠራ ሀሳብ ወደ ሀብት ለመለወጥ በሚደረገው ጥራት ስምምነቱ ፋይዳው የጎላ መሆኑን አብራርተዋል ። የፋሪስ ቴክኖሎጂ ግሩፕ መስራችና ዋና ስራ አስፈጻሚ ኤሊያስ ይርዳው በበኩላቸው አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ያለውን አምቅ አቅም ለመጠቀም ስምምነቱ መልካም አጋጣሚ መሆኑን ተናግረዋል። ግሩፑ ቴክኖሎጂ ነክ የሆኑ በርካታ ፕሮጀክቶች ቀርጾ እየሰራ መሆኑ ገልጸው፤ ስምምነቱ የፕሮጀክቶችን ውጤታማነት ይበልጥ ያሳድገዋል ብለዋል።
ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ተግባር ተኮር የስልጠናና የምርምር ስራዎችን በማከናወን ላይ ነው
Mar 18, 2024 112
ጋምቤላ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ) ጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ተግባር ተኮር የስልጠናና የምርምር ስራዎችን በማጠናከር ጥራቱን የጠበቀ የሰው ኃይልና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ለማፍለቅ እየሰራ መሆኑን አስታወቀ። የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ፣ የምርምር፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክትር ፓል ቦት ለኢዜአ እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው የትምህርት ጥራትና የምርምር ሪፎርም ስራዎችን በማጠናከር ብቃት ያለው የሰው ኃይልና ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን ለማፍለቅ እየሰራ ነው። ዩኒቨርሲቲው የሰው ሀብት ልማት፣ የምርምርና የማህበረሰብ አቀፍ አገልግሎት ተልዕኮውን ለመወጣት ሰፊ የሪፎርም ስራዎችን እያካሄደ እንደሚገኝ በማከል። በተለይም ዩኒቨርሲቲው ተግባር ተኮር ስልጠናዎችን በማጠናከር ተማሪዎችን ለመውጫ ፈተናው የማብቃት ስራዎችን ትኩረት ሰጥቶ እየተገበረ ነው ብለዋል። ከአሁን በፊት ሰልጣኞች በንድፈ ሀሳብ ላይ ብቻ ተወስነው ሲፈተኑ የነበሩባቸውን የምርምር ስራዎች ተግባር ተኮር በማድረግ የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ ቴክኖሎጂዎች ለማፍለቅም እየሰራ ስለመሆኑ ገልጸዋል። በተለይም የማህበረሰቡንና የመንግስትን የልማት ፖሊሲ ፍላጎትና አቅጫዎች ያገናዘቡ የግብርና፣ የማዕድን፣ የቱሪዝም፣ የሰላምና የጸጥታ የምርምር ዘርፎችን በመለየት ወደ ስራ መግባቱን ጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው በዘንድሮው ዓመት ለግብርና ተማሪዎች ተግባር ተኮር ሰርቶ ማሳያና ለምርምር የሚውል ሰፊ የእርሻ መሬት ወስዶ ወደ ስራ መግባቱንም ዶክተር ፓል ጨምረው ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የግብርና ትምህርት ክፍል መምህርና የእርሻ ስራ ተጠሪ መምህር ተሾመ ሞላ በበኩላቸው ከአሁን በፊት በግብርና ዘርፍ ተምረው ሲመረቁ የነበሩ ተማሪዎች የንድፈ ሃሰብ ስልጠና ብቻ ሲወስዱ እንደቆዩ ተናግረዋል፡፡ አሁን ላይ ግን ለሰልጣኞች በተግባርና በንድፈ ሃሳብ የተደገፈ ስልጠና ለመስጠት ዝግጅት መደረጉን ጠቁመው፤ እየታረሰ ያለው መሬትም ከሰርቶ ማሳያነት ባለፉ ለምርምርና ለገቢ ማስገኛነት ጭምር እንደሚያግዝ ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲው የጀመረው የግብርና ልማት ስራ በዝናብና በመስኖ የውሃ አማራጮች በመታገዝ እንደሆነም ገልጸዋል።
በመዲናዋ ዘመናዊ ቦዲ ካሜራዎች ተግባራዊ መደረጉ የትራፊክ እንቅስቃሴ ቁጥጥር ግልፀኝነት የተሞላበት የማድረግ ሥራን እያገዘ ነው
Mar 16, 2024 212
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ዘመናዊ ቦዲ ካሜራዎች ተግባራዊ መደረጉ የትራፊክ እንቅስቃሴ ቁጥጥርን ተጠያቂነትና ፍትሃዊነትን የማስፈን ሥራን እያገዘ ነው ሲል የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ። ከ400 በላይ ዘመናዊ ቦዲ ካሜራዎች ለትራፊክ ፖሊሶች ተከፋፍለው ሥራ ላይ ውለዋል። በትራፊክ እንቅስቃሴው ላይ የሚያጋጥሙ ችግሮችን በቴክኖሎጂ በተደገፈ አሠራር ለመፍታት የቦዲ ካሜራዎችን ቁጥር ለመጨመር እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል። ቦዲ ካሜራ ''በሕግ አስከባሪ አካላት ደንብ ልብሶችና በሌሎችም መሳሪያዎች ላይ የሚገጠም የካሜራ ቴክኖሎጂ'' በተለይ የሕግ ማስከበር ተግባራትን ውጤታማ ለማድረግ ይረዳል። ካሜራው ሕግ አስከባሪ አካላት በሥራ ላይ ባሉባቸው አካባቢዎች ያሉ እንቅስቃሴዎችን በመቅረጽ ከሕዝብ ጋር ያላቸውን ግንኙነት በሚገባ ለመቃኘት ያገለግላል። በአዲስ አበባ ፖሊስ የትራፊክ ቁጥጥር መምሪያ ምክትል ዳይሬክተር ኮማንደር ፈቃዱ ወንድምገዙ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ቦዲ ካሜራዎች ግልፀኝነት የተሞላበት አሠራር ለመፍጠር አጋዥ ናቸው። የአዲስ አበባ ፖሊስ ከሬዲዮ ጋር የተገናኙ ከ400 በላይ ዘመናዊ ቦዲ ካሜራዎችን ለትራፊክ ፖሊሶች በማከፋፈል የትራፊክ እንቅስቃሴውን እየተከታተለ መሆኑን ተናግረዋል። የቦዲ ካሜራዎቹ ትራፊክ ፖሊሱ ባለበት አካባቢ ያለውን አጠቃላይ ሁኔታ የሚቀርጹና የተለያዩ መረጃዎችንም መዝግበው የሚያስቀምጡ መሆኑን ገልፀዋል። በዚህም ከትራፊክ እንቅስቃሴ ጋር የተያያዙ ሥራዎች ተጠያቂነትና ፍትሃዊነትን ባረጋገጠ አግባብ እንዲከናወኑ ምቹ መደላድል መፈጠሩን ገልፀዋል። ከዚህ ቀደም ለትራፊክ መጨናነቅና ተያያዥ ችግሮች መፍትሔ የሚሰጠው በሬዲዮ በሚደረግ ግንኙነት እንደነበር አስታውሰው፤ አዳዲሶቹ ቦዲ ካሜራዎች የተሽከርካሪ ሁኔታዎችን ጨምሮ ሌሎች ወንጀሎችንም ለመቆጣጠር የሚያስችሉ ናቸው ብለዋል። ካሜራዎቹ በቀጥታ በማዕከል የሚመሩና ቁጥጥር የሚደረግባቸው ሲሆን፤ የትራፊክ ፍሰቱን ለማስተካከልና ለትራፊክ መጨናነቅም አፋጣኝ መፍትሔ ለመስጠት የሚያስችሉ መሆናቸውን አንስተዋል። ቴክኖሎጂው በአሽከርካሪዎችና በትራፊክ ፖሊስ መካከል ለሚፈጠሩ አለመግባባቶች በተጨባጭ ማስረጃ የተደገፈ መፍትሔ በመስጠት ችግሮችን ለመፍታት ማስቻሉንም ነው የገለጹት። ካሜራዎቹ ውጤታማ ሥራ እየተሰራባቸው ነው ያሉት ኮማንደር ፈቃዱ፤ የካሜራዎቹን ብዛት ካሉት የትራፊክ ፖሊሶች ቁጥር ጋር ለማጣጣም የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። የቂርቆስ ክፍለ ከተማ የትራፊክ ዲቪዥን ኃላፊ ኢንስፔክተር ያደሳ ሚደቅሳ፤ ቴክኖሎጂው በተለይ ለትራፊክ መጨናነቅ መፍትሔ ለመስጠት ሰፊ እገዛ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ካሜራዎቹ እያንዳንዱን ክስተት የተመለከተ ማስረጃ ስለሚያቀርቡ ማኅበረሰቡ እንግልት እንዳይደርስበት የሕግ አስከባሪ አካላትም ለተለያዩ ጫናዎች እንዳይዳረጉ ይረዳል ብለዋል። በአዲስ አበባ ፖሊስ የትራፊክ ቁጥጥር መምሪያ የሞተር እጀባና ቁጥጥር አባል ምክትል ኢንስፔክተር ኃይለማርያም ዘሪሁን በበኩላቸው፤ ቴክኖሎጂው መጀመሩ ዘርፉን አስተማማኝ ለማድረግ የሚረዳ መሆኑን ገልፀዋል። ችግሮችን ለመለየትና ለማስተካከል ምቹ መደላድል የሚፈጥር በመሆኑ የሕግ አስከባሪ አካላትን አፈጻጸም ለማሻሻል የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በኢትዮጵያ 4 ሚሊዮን የሚጠጉ ዜጎች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ሆነዋል - ብሔራዊ የመታወቂያ ፕሮግራም
Mar 15, 2024 276
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ 4 ሚሊዮን የሚጠጉ ዜጎች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት መሆናቸውን ብሔራዊ የመታወቂያ ፕሮግራም አስታወቀ። የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ባለፉት ጥቂት ዓመታት በተለያዩ መስሪያ ቤቶች በፕሮጀክት ደረጃ ሲተገበር ቆይቷል። የፕሮግራሙን ተቋማዊ አሰራርና ውጤታማነት ለማሳደግ የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ አዋጅ 1284/2015 በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጸድቆ ወደ ስራ መግባቱ ይታወቃል። የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የኮምዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አቤነዘር ፈለቀ በፕሮግራሙ አማካኝነት 4 ሚሊዮን የሚጠጉ ዜጎች የዲጂታል መታወቂያ ማግኘታቸውን ለኢዜአ ገልጸዋል። በፕሮግራሙ የተቀመጠውን ቅድመ ሁኔታ ለሚያሟሉ ነዋሪዎች ባለ 12 አሃዝ ልዩ የፋይዳ መለያ ቁጥር እንደሚሰጥና ይህ መለያ ቁጥር ያላቸው ሰዎች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ተደርገው እንደሚቆጠሩ አመልክተዋል። በ2016 በጀት ዓመት መጨረሻ የዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ ዜጎችን ቁጥር ወደ 10 ሚሊዮን ለማድረስ እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ዜጎች መታወቂያውን እንዲያገኙ ከማድረግ ባሻገር አገልግሎቱን ከተለያዩ ተቋማት ጋር የማስተሳሰር ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ነው ዳይሬክተሩ የገለጹት። የገቢዎች ሚኒስቴር፣ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት እንዲሁም የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ከዲጂታል መታወቂያ ጋር የተገናኘ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ጠቅሰዋል። በቅርቡም ኢትዮጵያ ለስደተኞች የዲጂታል መታወቂያ መስጠት መጀመሯን አስታውሰው በባንኮች የፋይናንስ ግብይትና መሰል አገልግሎቶችን በመታወቂያው የመስጠት ስራ ለማስፋት ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ትምህርት፣ ጤናና ማህበራዊ ዋስትና በቀጣይ አገልግሎቱ የሚተገበርባቸው መስኮች መሆናቸውንም ነው የጠቆሙት። የዲጂታል መታወቂያ ከተቋማት ጋር መተሳሰሩ የአገልግሎቱን ተጠቃሚ ቁጥር ለማሳደግ ፋይዳ እንዳለው አመልክተዋል። አቶ አቤነዘር ከዲጂታል መታወቂያ ጋር በተያያዘ በአንዳንዶች ዘንድ ብዥታዎች መኖራቸውን ጠቅሰው የዲጂታል መታወቂያው የተዘጋጀው የቀበሌ መታወቂያን ለመተካት አለመሆኑን ገልጸዋል። መታወቂያው የሚሰጠው አገልግሎት የቀበሌ መታወቂያን የሚመግብ እንጂ የሚተካ አይደለም ብለዋል። የዲጂታል መታወቂያ በኢትዮጵያ የሚኖር ማንኛውም ዜጋ የራሱን ማንነት የሚገልጽበት መለያ መሆኑን ተናግረዋል። የዲጂታል መታወቂያ ማውጣት አስገዳጅ ሊደረግ ነው የሚለው መረጃ ትክክል እንዳልሆነም ነው አቶ አቤነዘር የገለጹት። የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ አዋጅ ላይ ዜጎች መታወቂያውን የሚያወጡት በፈቃደኝነት ላይ ተመስረተው እንደሆነ በግልጽ እንደሚያስቀምጥ ጠቅሰው ተቋሙ ዜጎች መታወቂያውን በአስገዳጅነት እንዲያወጡ ማድረግ እንደማይችል ተናግረዋል። ይሁንና አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ለደንበኞቻቸው ለሚሰጡት አገልግሎት ዲጂታል መታወቂያን መጠቀምን እንደ ግዴታ ማስቀመጥ ይችላሉ ብለዋል። በዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ወቅት ከዜጎች የሚወሰዱ መረጃዎች ለሶስተኛ ወገን ተላልፈው እንደማይሰጡና ለዚህም የግል መረጃን መጠበቅ የሚያስችል የአሰራር ማዕቀፍ እንዳለ አንስተዋል። የዲጂታል መታወቂያ ሁሉም የሕብረተሰብ ክፍል አካታች በማድረግ ማንነታቸውን የሚገልጽ ማስረጃ እንዲይዙ ማድረግ የሚያስችል አማራጭ መሆኑን ዳይሬክተሩ አክለዋል። በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት 90 ሚሊዮን ዜጎችን የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ለማድረግ መታቃዱም ተገልጿል።
በክልሉ የኤሌክትሮኒክስ የመንግሥት ግዥ ሥርዓትን ተግባራዊ ለማድረግ መሰረተ ልማት እየተሟላ ነው
Mar 15, 2024 222
ሀዋሳ ፤ መጋቢት 6/2016(ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል የኤሌክትሮኒክስ የመንግስት የግዥ ሥርዓትን ለመተግበር አስፈላጊ መሰረተ ልማቶች እየተሟሉ መሆኑን የክልሉ የግዢና ንብረት አስተዳደር ኤጀንሲ አስታወቀ። የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ታሪኩ ቴፎ ለኢዜአ እንደገለጹት ኤጀንሲው የመንግሥት የግዥ ሥርዓትን ከሌብነት የጸዳና ውጤታማ ለማድረግ እየሰራ ነው። ከክልሉ በጀት ከ50 በመቶ በላይ የሚሆነው ለግዥ እንደሚውል ጠቁመው፣ በጀቱ በአግባቡ ለታለመለት ዓላማ እንዲውል የኤሌክትሮኒክስ የመንግስት የግዥ ሥርዓት ወሳኝ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። ለግዥ ሥርዓቱ ተግባራዊነት መሰረተ ልማት የማሟላት ሥራ ከወዲሁ እየተከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል። ዳይሬክተሩ እንዳሉት ኤጀንሲው ካለፈው መስከረም ወር ጀምሮ የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓትን ተግባራዊ ለማድረግ የቅድመ ዝግጅት ሥራ እያከናወነ ይገኛል። በተለይ ሂደቱን ለማፋጠን የመመሪያ፣ የህግ ማዕቀፍ እና አዋጅ የማሻሻል ሥራ ተከናውኖ በክልሉ ምክር ቤት ለማጽደቅ እየጠበቀ መሆኑን ጠቁመዋል። እንዲሁም በአገር ደረጃ የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት ሶፍትዌሩን ካበለጸገው ድርጅት ጋር ውል በመፈራረም አስፈላጊው መሰረተ ልማት የሟሟላት ሥራ መጀመሩን ጠቁመዋል። እየተከናወኑ ካሉ ሥራዎች መካከል የሶፍትዌር ማበልፀግ እና የኔትዎርክ ዝርጋታ ሥራዎች ተጠቃሽ መሆናቸውንም ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። የኤሌክትሮኒክ ግዥ አሰራር ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ሲደረግ በመንግስት ግዥ ስርዓት ውስጥ ግልጽነትና ፍትሃዊ ውድድር እንዲኖር ከማድረግ ባለፈ የነበሩ ብልሹ አሰራሮችን እንደሚያስቀር ተናግረዋል። ይህም የግዥ ሥርዓትን አሳታፊና ከሙስና የጸዳ ለማድረግ ፍቱን መሆኑን ጠቅሰው፣ በተለይ የወረቀት ጨረታንና የጥቅም ትስስርን ለማስቆም ሚናው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። አቶ ታሪኩ እንዳሉት የቅድመ ዝግጅት ስራውን ፈጥኖ በማጠናቀቅ ከ2017 በጀት ዓመት ጀምሮ በዘጠኝ የክልሉ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት በሙከራ ደረጃ ይጀመራል። በሙከራ ደረጃ የግዥ ሥርዓቱ ከሚተገበርባቸው ተቋማት መካከል ሀዋሳ ከተማ አስተዳደር፣ የክልሉ ፕሬዚዳንት ጽህፈት ቤት እና የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ይገኙበታል። ለእዚህም ለተለያዩ መስሪያ ቤቶች ባለሙያዎች በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስልጠና መሰጠቱን ነው የጠቆሙት። የሲዳማ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ከፍተኛ የግዢ ባለሙያ አቶ ዘሪሁን አሰፋ የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ሥርዓቱ ተግባራዊ ሲደረግ በግዥ ስርአቱ አሁን እየታዩ ያሉ ችግሮችን ያስተካክላል። እስካሁን ሲሰራበት የቆየው የማንዋል ግዥ አድካሚ፣ ብዙ ጊዜ የሚጠይቅ፣ ግልጽነት የጎደለው፣ ለሙስና የተጋለጠ እና የተደራሽነት ችግር ያለበት መሆኑን አስረድተዋል። የኤሌክትሮኒክስ የመንግስት የግዥ ሥርዓቱ ይህንን ችግር ሙሉ ለሙሉ ከማስወገድ ባለፈ የግዥ ስርአቱን ወጤታማ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ሥርዓት ቴክኖሎጂን በመጠቀም ግዥ ፈጻሚ መሥሪያ ቤቶች በኦንላይን ለሚያወጡት ግዥ ጨረታ ተጫራቾም በኦንላይን እንዲጫረቱ የሚያስችል ዘዴ ነው።
የሀገር በቀል እውቀቶችን መረጃ የማሰባስብና የመሰነድ ስራ እየተከናወነ ነው-የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር
Mar 14, 2024 216
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2016(ኢዜአ)፦ የሀገር በቀል እውቀቶችን መረጃ የማሰባስብና የመሰነድ ስራ እየተከናወነ መሆኑን የኢኖቬሸንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር "አገር በቀል እውቀት ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ለሁለንተናዊ እድገት" በሚል መሪ ሀሳብ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ምክክር አካሂዷል። የሀገር በቀል እውቀቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ፣ ሀገር በቀል እውቀት በቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ዘርፍ ያላቸው ምቹ ሁኔታ እና ተግዳሮት ላይ ያተኮሩ ፅሑፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል። በኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር መሪ ስራ አስፈጻሚ ተክለማሪያም ተሰማ (ዶ/ር) ኢትዮጵያውያን አገር በቀል እውቀቶችን ለችግሮቻቸው መፍትሄ አድርገው ሲጠቀሙ መኖራቸውን አውስተዋል። ሆኖም ሀገር በቀል እውቀቶችን በሳይንሳዊ መንገድ እና በቴክኖሎጂ የተደገፉ ከማድረግ አንጻር ውስንነቶች መኖራቸውን አንስተው፥ በተገቢው መልኩ ተሰንደው አለመቀመጣቸውንም ተናግረዋል። ሚኒስቴሩ አገር በቀል እውቀቶችን ከቴክኖሎጂ ጋር በማስተሳሰር የሀገሪቱን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የአገር በቀል እውቀት ክፍል ማቋቋሙን ገልጸዋል። በዚህም የሀገር ሀብት የሆኑ አገር በቀል እውቀቶችን የማሰባሰብ እና የመለየት፣ ጥቅማቸውን የመተንተን እና በአግባቡ የማደራጀት ስራን እያከናወነ ሲሆን በቀጣይ ከቴክኖሎጂ ጋር እንዲተሳሰሩ ይደረጋል ብለዋል። የተጀመረው ስራ ውጤታማ እንዲሆንም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እና የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፋርማሲ ፕሮፌሰር አርዓያ ሀይመተ ሳህለድንግል፥ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በመሰነድ ረገድ ክፍተቶች እንዳሉ ጠቅሰው ችግሩን ለመቅረፍ የጋራ ጥረት ያስፈልጋል ብለዋል። በደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የአንኮበር የእጽዋትና ሀገር በቀል እውቀት ማእከል አስተባባሪ ዶክተር አማረ አያሌው በበኩላቸው፥ የባህል ህክምና መረጃን የመሰነድ፣ ለመድሃኒትነት የሚውሉ እጽዋትን መንከባከብ ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ የመሬት ሀብትን በዘመናዊ እና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ለማስተዳደር እየተሰራ ያለው የዲጂታላይዜሽን እና የሪፎርም ስራ ተመልክቼአለሁ -ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Mar 10, 2024 289
አዲስ አበባ፤መጋቢት 1/2016 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ መሬትን በዘመናዊ እና ፍትሃዊ መንገድ ለማስተዳደር በመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ የተቀየሰው የዲጂታላይዜሽን እና የሪፎርም ስራን መመልከታቸውን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባዋ ይህን ያሉት በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልእክት ነው ፤ በአዲስ አበባ ከተማ ውስን ሃብት የሆነውን መሬትን በዘመናዊ እና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ለማስተዳደር በመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ እየተሰራ ያለው የዲጂታላይዜሽን እና የሪፎርም ስራን የመስክ ምልከታ ማድረጋቸውን ገልጸዋል:: ይህም በዘርፉ ላይ ያለውን የባለ ጉዳይ እንግልት እና ብልሹ አሰራሮችን በማስቀረት ለተገልጋዮች ቀላልና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል :: የዲጂታላይዜሽን ስራው ከማዕከል እስከ ክፍለ ከተሞች ያለውን መሬት በአንድ ማዕከል ማስተዳደር አቅም የሚፈጥር መሆኑን ሲጠቅሱ ሲስተሙ በየደረጃ ያለውን አገልግሎት ክትትል በማድረግ ተገልጋዮች ፍትሃዊ እና ቀልጣፋ አገልግሎት አንዲያገኙ የሚያስችል አንደሆነ ተናግረዋል::
ኢትዮ-ቴሌኮም በአድዋ ድል መታሰቢያ የተሞክሮ ማዕከል ከፈተ
Mar 9, 2024 314
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮ-ቴሌኮም ደንበኞቹ ዘመኑ ያፈራውን ቴክኖሎጂዎች የሚጎበኙበትና በተግባር የሚሞክሩበት ማዕከል በአድዋ ድል መታሰቢያ ከፈተ። ማዕከሉ የግለሰብና የድርጅት ደንበኞች ምርትና አገልግሎቶችን የሚመለከቱበት፣ አዳዲስ ዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በተግባር በመሞከር የፈጠራ ሥራቸውን የሚያነሳሱበትና የቴክኖሎጂ ግኝቶችን የሚመራመሩበት መሆኑ ተመላክቷል። ማዕከሉ የቴሌኮም ቴክኖሎጂ ያለፈባቸውን በርካታ ሂደቶች የሚዘክርና አሁን ላይ የደረሰበትን የዕድገት ደረጃ የሚያሳይ እንዲሁም የወደፊቱን የቴክኖሎጂ እድገት የሚያመላክት መሆኑንም እንዲሁ። የኢትዮ ቴሌኮምን የዕድገት ደረጃዎች የሚተርኩና የሚያስቃኙ የቴሌኮም መሳሪያዎችን ጨምሮ አሁን የደረሰበትን የቴክኖሎጂ ልህቀት በሚያሳይ መልክ መደራጀቱንም ተጠቅሷል። ዘመኑ ያፈራቸውን የተለያዩ የረቀቁ የቴክኖሎጂ ትሩፋቶችን ለአብነትም እጅግ ፈጣን የ5ጂ ኮኔክቲቪቲ ቨርቹዋል ሪያሊቲ፣ የፈጠራ ሶሉሽኖችን፣ የስማርት ሆም አውቶሜሽን፤ የቴሌብር ፋይናንሺያል ግብይቶችንና የፋይናንሺያል ቴክኖሎጂ ትስስርን ማካተቱ ተገልጿል። ስማርት የቱሪዝም አገልግሎቶችን፣ የርቀት ታካሚ ክትትልን፣ የስማርት ግብርና ቴክኒኮችን፣ ስማርት የትምህርትና የትምህርት መሳሪያዎችን፤ ስማርት የማዕድን ልማትን፣ የክላውድና የዳታ ማዕከል ሶሉሽንስ፣ ፈጣንና ሙሉ ጊዜ የደህንነት ቁጥጥር ሶሉሽን እንዲሁም በመዝናኛው ዘርፍ በ5 ጂ የታገዘ የሙዚቃ መዝናኛ ሶሉሽንንና በመሳሰሉ አዳዲስ የቴክኖሎጂ ውጤቶች የተሞላ ማዕከል ነው ተብሏል።
ለዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም መሳካት መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ያደርጋል- አቶ ተመስገን ጥሩነህ
Mar 9, 2024 322
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30/2016(ኢዜአ)፦ለዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም መሳካት መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ማድረጉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው እንዳስታወቁት ብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም እስከ አሁን የደረሰበትን ደረጃ፣ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት፣ የወደፊት ዕቅዶችና የስራውን ሒደት በተቋሙ ተገኝተው ጎብኝተዋል። ብሔራዊ መታወቂያ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራተጂ ውስጥ ለኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ አስቻይ ሁኔታ ተብለው ከተቀመጡ ስትራተጂዎች አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል። ዲጂታል መታወቂያ የዜጎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት እና አገልግሎት የማግኘት ቅልጥፍናን ለማረገጥ አይነተኛ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል። የዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ መሆን ለእያንዳንዱ ዜጋ አስፈላጊ በመሆኑም ለፕሮግራሙ መሳካት መንግስት ተገቢውን ድጋፍና ክትትል ማድረጉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል።
በሶማሌ ክልል 900 ቤተሰቦችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የፀሐይ ኃይል (ሶላር) መብራት ግንባታ ፕሮጀክት ተጠናቀቀ
Mar 8, 2024 300
ጅግጅጋ፤ የካቲት 29/2016 (ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል 900 ቤተሰቦችን ተጠቃሚ የሚያደርግ በፀሐይ ኃይል የሚሰራ (ሶላር) መብራት ግንባታ ፕሮጀክት ማጠናቀቁን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኢነርጂ ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ የተመራ የፊዴራልና የክልሉ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች ቡድን ፕሮጀክቱን ጎብኝቷል። ሚኒስትር ዴኤታው በጉብኝቱ ላይ እንደገለጹት፤ በክልሉ ዋርዴር ወረዳ ኩርቱኒ ቀበሌ የሚገኘው የፀሐይ ኃይል ኤሌክትሪክ ማምረቻ ፕሮጀክት ግንባታና የሶላር ተከላ ስራ ሙሉ በመሉ ተጠናቋል። ፕሮጀክቱ 140 ኪሎ ቮልት የማመንጨት አቅም ያለው በመሆኑ ለመኖሪያ ቤቶች፣ ለማምረቻ ተቋማት፣ ለጤና፣ ለትምህርትና ለመንግስታዊ ተቋማት በቂ ኃይል ማቅረብ እንደሚችል ገልጸዋል። ከመንግሥት በተመደበ 63 ሚሊዮን ብር ወጪ የተጀመረው ፕሮጀክቱ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ውስጥ መሥመር ተዘርግቶለት አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምርም አስታውቀዋል። የኩርቱኒ ቀበሌ ነዋሪው አቶ አብዲ ኤሪኮ በሰጡት አስተያየት፤ ፕሮጀክቱ የቀበሌያቸው ነዋሪዎችን ከጨለማ እንደሚያወጣቸው ገልጸው ቀሪ ስራዎች በቶሎ ተጠናቀው አገልግሎቱ እንዲጀመሩ ጠይቀዋል ። በሚኒስትር ዴኤታው የሚመራው ቡድን ከሶማሌ ክልል በተጨማሪ በሐረሪ፣ በኦሮሚያና በሌሎች ክልሎች የፀሐይ ኃይልና የባዮጋዝ ቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶችን የሥራ እንቅስቃሴ እንደሚጎበኝም ታውቋል።
ኢትዮ ቴሌኮም በዲጂታል አካታችነት ሴቶችን ማብቃት የሚያስችል ስምምነት “ኮኔክትድ ውሜን” ከተባለ ኢኒሼቲቭ ጋር ተፈራረመ
Mar 8, 2024 148
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮ ቴሌኮም በዲጂታል አካታችነት ሴቶችን ማብቃት የሚያስችል ስምምነት “ኮኔክትድ ውሜን” ከተባለ ኢኒሼቲቭ ጋር ተፈራርሟል። ስምምነቱ የዲጂታል ስርዓተ-ፆታ ልዩነትን ለማጥበብ እና የሴቶችን የዲጂታል ተካታችነት ማሳደግ የሚያስችል መሆኑ ተጠቁሟል። ስምምነቱን የኢቲዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ከኢኒሼቲቩ የስራ ሃላፊዎች ጋር በስፔን ባርሴሎና መፈረማቸውን ከኢቲዮ ቴሌኮም የተገኘው መረጃ ያመላክታል። ስምምነቱ የሴቶችን የሞባይል ኢንተርኔት እና የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት/ቴሌብር/ ተጠቃሚ ቁጥር እ.ኤ.አ እስከ 2026 በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ ያለመ ሲሆን አካታች የሞባይል ኢንተርኔት እና የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎቶች ማቅረብን ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡ ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ እንዳሉት ኩባንያው አሁን የሚታየውን የዲጂታል ስርዓተ-ፆታ ክፍተት ለማጥበብ የሞባይል ኢንተርኔትና የሞባይል ፋይናንሺያል አገልግሎቶችን ለሴቶች ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ ሴቶች በዲጂታል ኢኮኖሚው ንቁ ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑ ተገልጿል።
ኦቪድ ግሩፕ የትራንስፖርት ችግርን ለመፍታት የሚያስችል የኬብል ካር ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ሊያደርግ ነው
Mar 7, 2024 254
አዲስ አበባ፤ የካቲት 28/2016(ኢዜአ)፦ ኦቪድ ግሩፕ የትራንስፖርት ችግርን ለመፍታት የሚያስችል የኬብል ካር (በገመድ ላይ ተንጠልጣይ የህዝብ ትራንስፖርት) ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ሊያደርግ መሆኑን የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዮናስ ታደሰ ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነትና ለልማቱ ባላቸው ቁርጠኝነት በተለያዩ አካባቢዎች እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶች ሀገሪቷን በብዙ መልኩ ወደ ፊት የሚያራምዱ ናቸው ብለዋል። በሀገራዊ ልማትና በተለይም በግንባታው ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን በተመለከተ ኢዜአ ከኦቪድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዮናስ ታደሰ ጋር ቆይታ አድርጓል። ስራ አስፈጻሚው በማብራሪያቸው፣ ኦቪድ ግሩፕ በቴክኖሎጂ የታገዙ ዘመናዊ ቤቶችን ከመገንባት ባሻገር የትራንስፖርት ችግርን ለመፍታት በአዲስ አበባ የኬብል ካር ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ሊያደርግ መሆኑን ገልጸዋል። በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገርና ገበታ ለትውልድ የኢትዮጵያን ገጽታ የሚያጎሉ የተለያዩ ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረው፣ ኦቪድ ግሩፕም በግንባታው ዘርፍ አዳዲስ ቴክኖሎጂ በመጠቀም ዘመናዊ ከተማ ለመገንባት በመንግስት የሚደረገውን ጥረት የበለጠ የሚደግፍ መሆኑን አረጋግጠዋል። ኦቪድ ግሩፕ በቴክኖሎጂ የታገዙ ዘመናዊ ቤቶችን ከመገንባት ባሻገር የትራንስፖርት ችግርን ለመፍታት በአዲስ አበባ የኬብል ካር ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ለማድረግ የፕሮጀክት ጥናት ማጠናቀቁን ይፋ አድርገዋል። የባቡር እና የመኪና መሰረተ ልማቶችን ማፍረስ ሳያስፈልግ በገመድ ላይ ተንጠልጣይ የህዝብ ትራንስፖርት ወይም ኬብል ካር ቴክኖሎጂን በአዲስ አበባ ተግባራዊ ለማድረግ ያሰችላል ብለዋል። መንግስት አቅመ ደካማና አነስተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ኑሮ ለማሻሻል የሚያደርገውን ጥረት አድንቀው ለስኬታማነቱ ኦቪድ እገዛና ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በመንግስት እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶች የከተማዋን ገጽታ ከማሳመር ባለፈ የነዋሪዎችን ሕይወት የሚቀይሩና ተጠቃሚ የሚያደርጉ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ኦቪድ በዚህ ረገድ ከመንግስት ጋር በመተባበር የራሱን አሻራ እያሳረፈ ይገኛል ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር የአዋሬ መንደር ልማት እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አመራር፣ በሺዎች ለሚቆጠሩ እናቶች የስራ ዕድል የፈጠረ የእንጀራ መጋገሪያ ማዕከል በመገንባት ኦቪድ መሳተፉን አንስተው ከግንባታ ባሻገር ማህበራዊ ሃላፊነቱን በተጠናከረ መልኩ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል። በሁሉም የልማት መስኮች የመንግስትና የግል ዘርፍ አጋርነት እየተጠናከረ መምጣቱን የጠቀሱት አቶ ዮናስ፤ በተለይም የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብና ቁርጠኝነት ሀገሪቷን ወደ ፊት የሚያራምድ ስለመሆኑ አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገራዊ ዕምቅ ጸጋዎችን በማልማት ከገበታ ለሸገር እስከ ገበታ ለትውለድ ተግባራዊ ያደረጓቸው ፕሮጀክቶች ሁነኛ ማሳያ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። የኦቪድ የቤት ግንባታ አካሄድ በተለይም አነስተኛና መካከለኛ ገቢ ያለውን ብዙሃኑን የሕብረተሰብ ክፍል በተመጣጣኝ ዋጋ፣ በአጭር ጊዜና በጥራት በመገንባት ተጠቃሚ ማድረግ መሆኑንም አስረድተዋል። በመኖሪያ ቤት ግንባታ ስራ አሁን እየተጠቀመ ካለው ቴክኖሎጂ ባለፈ በቅርቡ ሌላ ዘመናዊ የግንባታ ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ለማድረግ መዘጋጀቱንም ገልጸዋል። በመሆኑም ኦቪድ ሀገራዊ ልማትን ከማገዝ ባለፈ በግንባታው ዘርፍ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የመጠቀምና በአጭር ጊዜ የማጠናቀቅ ስራውን ይቀጥላል ብለዋል።
የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የሚኖረውን ሚና በውል ተረድቶ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ
Mar 5, 2024 230
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 26/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ የተጀመሩ ስራዎችን ለማጠናከር የሰው ሰራሽ አስተውሎት በውጭ ግንኙነት እና በደህንነት ላይ ያለውን ሚና በውል ተረድቶ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ። በውጪ ጉዳይ ኢንስቲትዩት አዘጋጅነት "ዓለም አቀፋዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አስተዳደር ስርዓት ጅምሮች እና የኢትዮጵያ ትልም" በሚል መሪ ሀሳብ የፖሊሲ ምክክር መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን ዓለማየሁ፣ የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጃፋር በድሩ፣ እንዲሁም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጽህፈት ቤት ኃላፊ አምባሳደር እሸቴ ጥላሁን ተገኝተዋል። የመድረኩ ዓላማም የሰው ሰራሽ አስተውሎት በውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ ተልእኮ ላይ ያለውን ጠቀሜታ እና ተጽእኖ ማስገንዘብ መሆኑ ተገልጿል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጽህፈት ቤት ኃላፊ አምባሳደር እሸቴ ጥላሁን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ የሰው ሰራሽ አስተውሎት በተለያዩ መስኮች የዓለምን አሰላለፍ እየቀየረ ነው። ቀደም ካሉ የቴክኖሎጂ አብዮቶች የላቀ ውጤት እንደሚያመጣ የታመነበት መሆኑን ገልጸው፥ በዚህም የአገራት የበላይነት እና ተከታይነት አይቀሬ መሆኑ እየታየ ነው ብለዋል። በዚህም ምክንያት በአገራት መካከል በጉዳዩ ላይ ድርድሮች መጀመራቸውን ገልጸዋል። አፍሪካ በዓለም መድረክ ጥቅሟን እንድታስከብር እንደ ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎትን አጀንዳ ቀደም ብለው ያነሱ አገራት የመሪነት ሚና እንዲጫወቱ እድል የሚፈጥር መሆኑንም ተናግረዋል። ከዚህ እኳያ እንደ ሀገር ሊኖር ስለሚገባው ዝግጅት እና መያዝ ስላለበት አቋም በጥናት ላይ የተመሰረተ አካሄድን መቅረጽ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅ ረገድ የሰው ሰራሽ አስተውሎት በውጭ ግንኙነት እና በደህንነት ላይ ያለውን ሚና በውል ተረድቶ መስራት እንደሚገባ ጠቁመዋል። እንዲሁም በምህዳሩ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመገኘት ቴክኖሎጂውን መከታተል እና የተጀመሩ ስራዎችን ማጠናከር ይገባል ነው ያሉት። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጃፋር በድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ኢንስቲትዩቱ ለኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ መዳበር የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። በሰው ሰራሽ አስተውሎት የሀገሪቱ የውጪ ግንኙነትና ዲፕሎማሲ እንዲዳብር እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፥ የአስተዳደር ስርዓቱም ሀገራዊ ጥቅምን የሚያስጠብቅ እንዲሆን መስራት ያስፈልጋል ብለዋል። ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ ቴክኖሎጂን ለተለያዩ አገልግሎቶች በመጠቀም ላይ እንደምትገኝ ገልጸው ቴክኖሎጂውን በመረዳት የሚመጣውን አሉታዊ ተጽእኖ መቆጣጠር እንደሚገባ አንስተዋል። ኢትዮጵያ ዲጂታላይዜሽንን እውን ለማድረግ ስትራቴጂ ቀርጻ ተግባራዊ እያደረገች ነው ያሉት ደግሞ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን ዓለማየሁ ናቸው። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የዲጂታል መሰረተ ልማቶችን በመገንባት ረገድ ከፍተኛ ውጤት የተመዘገበበት መሆኑን ገልጸው፥ ይህም የዲጂታል ስነ ምህዳሩ እንዲያድግ ማስቻሉን ተናግረዋል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት የዲጂታል ሽግግርን ለማሳለጥ ቁልፍ መሳሪያ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፥ ጥቅም ላይ ሲውል በማስተዋል እና በጥንቃቄ መሆን እንዳለበት አስገንዝበዋል። ሚኒስቴሩ የሰው ሰራሽ አስተውሎት እንዲያድግ እንዲሁም ኃላፊነት የተሞላበት አጠቃቀም እንዲኖር በቁርጠኝነት እየሰራ እንደሚገኝ አመላክተዋል።
ቁልፍ ለሆኑ የመንግሥትና የሕዝብ ተቋማት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ የሳይበር ደኅንነት ጥበቃ እየተደረገ ነው
Mar 5, 2024 260
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2016(ኢዜአ)፦ ቁልፍ ለሆኑ የመንግሥትና የሕዝብ ተቋማት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ የሳይበር ደኅንነት ጥበቃ እየተደረገ መሆኑን የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ገለጸ፡፡ የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ከኢትዮጵያ ሳይበር ደኅንነት ማኅበር ጋር ያዘጋጁት የሳይበር ደኅንነትና ዲጂታል ሽግግር ጉባዔ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው፡፡ የኢትዮጵያን የሳይበር ደኅንነትና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ ብሎም ሀገራዊ የሳይበር ሥነ-ምህዳር ለማጠናከር ኮንፍረንሱ ዓይነተኛ ሚና ይጫወታል ተብሏል፡፡ የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ፤ ተቋሙ ቁልፍ የሆኑ የመንግሥትና የሕዝብ ተቋማትን የሳይበር ደኅንነት የማስጠበቅ ተልዕኮ በብቃት እየተወጣ ይገኛል ብለዋል፡፡ በተለይም ትላልቅና ወሳኝ የሆኑ መሠረተ-ልማቶችን፣ የፋይናንስና የሚዲያ ተቋማትን እንዲሁም ሌሎች የሳይበር ደኅንነት ጥበቃ በንቃት እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። የሳይበር ጥቃት መነሻዎች የተለያዩ ቦታዎች መሆናቸውን የገለጹት ዳይሬክተሯ፤ የመከላከሉ ሥራም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የሳይበር ደኅንነትን በተመለከተ በማኅበረሰቡ ዘንድ ሰፊ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን አለማየሁ፤ የ2025 ዲጂታል ኢትዮጵያን ለማስተግበር በዘመናዊ የዲጂታል ሽግግር የሳይበር ደኅንነትን ማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን ገልፀዋል። የሳይበር ሥርዓቱን ደኅንነት ማስጠበቅ የአንድ ተቋም ኃላፊነት ብቻ አለመሆኑን ጠቅሰው፤ ተቋማትና ግለሰቦችም የበኩላቸውን ሚና ሊወጡ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሳይበር ደኅንነት ማኅበር እየሰራ ላለው በጎ ተግባር ሚኒስቴሩ የሚደግፈውና የሚያበረታታው መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የኢትዮጵያ የሳይበር ደኅንነት ማኅበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ብርሃኑ በየነ፤ ጉባዔው የኢትዮጵያን የሳይበር ደኅንነትና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ ብሎም ሀገራዊ የሳይበር ሥነ-ምህዳርን ለማጠናከር እንደሚረዳ ገልፀዋል፡፡ ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ጉባዔ የሳይበር ደኅንነት፣ የሳይበር ሕግ እና ተያያዥ ርዕሰ-ጉዳዮች ዙሪያ ከ12 በላይ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት እንደሚካሄድባቸውም ጠቁመዋል፡፡ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሳይበር ጥቃቶችና ተጋላጭነቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመምጣቱ በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት ከተሰነዘሩ 4ሺህ 623 የሳይበር ጥቃቶች 98 በመቶውን ማክሸፍ መቻሉ ይታወቃል። የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል በተከናወኑ ተግባራት በአጠቃላይ ከ10 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ማዳን ተችሏል።
"ዓለም አቀፋዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አስተዳደር ስርዓት ጅምሮች እና የኢትዮጵያ ትልም" ላይ ያተኮረ ምክክር እየተካሄደ ነው
Mar 5, 2024 281
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2016 (ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፋዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አስተዳደር ስርዓት ጅምሮች እና የኢትዮጵያ ትልም" በሚል ርዕሰ ጉዳይ ላይ የፖሊሲ ምክክር እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን ዓለማየሁ፣ የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጃፋር በድሩ፣ እንዲሁም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጽህፈት ቤት ኃላፊ አምባሳደር እሸቴ ጥላሁን ተገኝተዋል። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲቲዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጃፋር በድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ኢንስቲትዩቱ ለኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ መዳበር የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። በዚህም በዘርፉ ችግር ፈቺ የሆኑ ሀሳቦችን እያመነጨ መሆኑን ጠቅሰው፥ የዛሬው የውይይት መድረክም የዚሁ አካል መሆኑን ገልጸዋል። የመድረኩ ዓላማም የሰው ሰራሽ አስተውሎት በውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ ተልእኮ ላይ ያለውን ጠቀሜታ እና ተጽእኖ ማስገንዘብ መሆኑን ገልጸዋል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት በየጊዜው እያደገ መሆኑ ስጋትንም ይዞ መምጣቱን ጠቅሰው ከዚህ አኳያ ኢትዮጵያ በዘርፉ በንቃት መሳተፍ እንደሚገባት ጠቁመዋል።
የሳይበር ደህንነትና የዲጂታል ሽግግር ጉባኤ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀመረ
Mar 5, 2024 159
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2016(ኢዜአ)፡- የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ከኢትዮጵያ ሳይበር ደህንነት ማህበር ጋር ያዘጋጁት የሳይበር ደህንነትና ዲጂታል ሽግግር ጉባኤ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። ጉባኤው የኢትዮጵያን የሳይበር ደህንነትና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅና ሀገራዊ የሳይበር ሥነ-ምህዳር ማጠናከር ላይ በስፋት እንደሚመከርበት ተጠቁሟል። ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ጉባኤ የሳይበር ደህንነት፣ የሳይበር ህግ እና ተያያዥ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ ከ12 በላይ ጥናታዊ ፅሑፎች ቀርበው ውይይት እንደሚደረግባቸው ተገልጿል። ጉባኤው ማህበረሰቡ ስለ ሳይበር ደህንነት ግንዛቤ እንዲኖረው የማድረግ ዓላማ እንዳለውም ተጠቁሟል። በጉባኤው የመክፈቻ መርሃ ግብር ላይ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግሥት ሃሚድ፣ የኢትዮጵያ ሳይበር ደህንነት ማህበር ፕሬዚዳንት ዶክተር ብርሃኑ በየነን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው የዘርፉ አመራሮችና ተመራማሪዎች ተገኝተዋል።
የሳይበር ደህንነትና የዲጂታል ሽግግር ጉባኤ ነገ በአዲስ አበባ ይጀመራል
Mar 4, 2024 126
አዲስ አበባ፤ የካቲት 25/2016(ኢዜአ)፡- የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ከኢትዮጵያ ሳይበር ደህንነት ማህበር ጋር የሚያዘጋጁት ሁለተኛው የሳይበር ደህንነትና ዲጂታል ሽግግር ጉባኤ ነገ በአዲስ አበባ ይጀመራል። ሁለቱ ተቋማት በሰጡት መግለጫ፥ ለሁለት ቀናት በሚካሄደው በዚህ ጉባኤ የሳይበር ደህንነት፣ የሳይበር ህግ እና ተያያዥ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ ፅሑፎች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል ብለዋል። ጉባኤው ማህበረሰቡ ስለሳይበር ደህንነት ግንዛቤ እንዲኖረው የማድረግ ዓላማ እንዳለውም ገልጸዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ማህበረሰቡ በሳይበር ደህንነት ዙሪያ የተሻለ አረዳድ እንዲኖረው እየሰራ ስለመሆኑም ጠቁሟል።
በዓመት ለኔትወርክ ግዢ የሚወጣውን 60 ሚሊየን ዶላር ማስቀረት የሚያስችል ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ ነው
Mar 1, 2024 437
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2016(ኢዜአ)፦ ሀገሪቱ በዓመት ለኔትወርክ ግዢ የምታወጣውን 60 ሚሊየን ዶላር ማስቀረት የሚያስችል ብሔራዊ የኔትዎርክ ማሳለጫ ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። ለአንድ ሳምንት ሲካሔድ የቆየው ሀገራዊ የዲጂታል አቅሞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሳምንት'ዛሬ ተጠናቋል። መርሃ ግብሩ ሀገሪቱ ያላትን የቴክኖሎጂ አቅም አሟጦ ለመጠቀምና በዘርፉ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመፍታት ያለመ ነው ተብሏል። በመርሃ ግብሩ ላይ በሚኒስቴሩ የብሔራዊ ኔትወርክ ፕሮጀክት መሪ አቶ ዳንኤል አድነው የፕሮጀክቱን አስፈላጊነት የሚዳስስ ጽሁፍ አቅርበዋል። ኢትዮጵያ እየተጠቀመች ያለው ኢንተርኔት ቨርዠን ፕሮቶኮል አለም የደረሰበት የቴክኖሎጂ ደረጃ ላይ ለመድረስ አዳጋች እንዲሆን አድርጎታል ብለዋል። በተጨማሪም በቀላሉ መልማት የሚችል የኔትወርክ ስርጭት እያለ ሀገሪቱ ለኔትወርክ ብቻ አላስፈላጊ ወጪ እንድታወጣና ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭ እንድትሆን አድርጓቷል ነው ያሉት። ተግባራዊ የሚደረገው ብሔራዊ የኔትዎርክ ማሳለጫ ፕሮጀክት ሀገሪቱን ከአላስፈላጊ ወጪና ከሳይበር ጥቃት የሚታደግ ነው ብለዋል። ፕሮጀክቱን በሙከራ ደረጃ በማልማት ተግባራዊ መደረጉን ገልጸው፤ በቀጣይ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ተደራሽ በማድረግ የኢንተርኔት አገልግሎቱን ፈጣንና ቀልጣፋ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። ፕሮጀክቱ በሀገሪቱ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች በቴክኖሎጂ እንዲደገፉ ለማድረግ፣ በትምህርት ስርዓቱ ላይ የተጀመረውን ቴክኖሎጂያዊ አሰራር ለማጠናከርና ተቋማት የሚሰጡትን አገልግሎቶች ለማቀላጠፍ የሚያግዝ ነው ብለዋል። ፕሮጀክቱ ሙሉ በመሉ ተግባራዊ ሲሆን በዋናነት እየተስፋፋ የመጣውን የሳይበር ጥቃት 80 በመቶ ለመቀነስ የሚያስችል መሆኑንም አክለዋል። እንዲሁም ለኢንተርኔት ግዢ ሀገሪቱ በዓመት የምታወጣውን ከ60 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ማዳን ያስችላል ነው ያሉት። ብሔራዊ የኔትዎርክ ማሳለጫ ፕሮጀክት የተለያዩ የሙከራ ስራዎች ተደርጎለት ስኬታማ በመሆኑ በቅርቡ ተግባራዊ እንደሚደረግም አረጋግጠዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን አለማየሁ በበኩላቸው ሀገራዊ የዲጂታል አቅሞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሳምንት በዲጂታል እና በአይሲቲ ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራትን ለማስተዋወቅ የተካሔደ ነው። በተጨማሪም ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሒደት ውስጥ ሀገሪቱ በዘርፉ ያላትን አቅም ለማስገንዘብና ቴክኖሎጂን አሟጦ ለመጠቀም የሚያግዝ እንደነበርም ገልጸዋል። በአጠቃላይ የዲጂታል ስርዓቱን ይበልጥ ተደራሽ በማድረግ ግብይቱን ለማስፋትና ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
የከተሞች ፎረም መዘጋጀቱ ችግር ፈቺ አዳዲስ የፈጠራ ሥራዎቻችንን ለማስተዋወቅ ዕድል ፈጥሮልናል - ተሳታፊዎች
Feb 25, 2024 383
ሶዶ፤ የካቲት 17/2016(ኢዜአ)፦ በዘጠነኛው የከተሞች ፎረም ላይ መሳተፋቸው የህብረተሰቡን ችግር የሚያቃልሉ አዳዲስ የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ለማስተዋወቅ ዕድል እንደፈጠረላቸው በፎረሙ ላይ የተሳተፉ ሥራ ፈጣሪዎች ገለጹ። ከየካቲት 9 እስከ 15/2016 በወላይታ ሶዶ በተካሄደው 9ኛው የከተሞች ፎረም ላይ የተሳተፉ ሥራ ፈጣሪዎች እንደገለጹት በፎረሙ የተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች መሳተፋቸው አብሮነትን ለማጠናከር የሚያስችል ነው። የህብረተሰቡን ችግር የሚያቃልሉ አዳዲስ የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ለማስተዋወቅ ፎረሙ የተሻለ ዕድል እንደፈጠረላቸውም ለኢዜአ ገልጸዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ሥራ ፈጣሪዎች መካከል የወራቤ ከተማ ነዋሪው አቶ ረሻድ ከድር በእናቶች እና አርሶ አደሮች ላይ የሚስተዋለውን የሥራ ጫና ማቃለል የሚያስችል የእንሰትና የቆጮ መፋቂያ፣ የጤፍ መውቂያ እንዲሁም የቃጫ ማምረቻ ማሽኖች ማቅረባቸውን ጠቅሰዋል። ይህም የፈጠራ ሥራዎቻችንን ለማስተዋወቅ የተሻለ እድል ፈጥሮልናል ሲሉም ገልጸዋል። በወላይታ ዞን የአረካ ከተማ ነዋሪውና በአውደ ርዕዩ ላይ የሰራውን መኪና ይዞ የቀረበው ወጣት አጃዬ ማጆር በበኩሉ ፎረሙ ያለንን የፈጠራ ውጤት ለሌሎች ለማስተዋወቅ ረድቶናል ብሏል። የባለ ሁለት እግር ሞተር ሳይክል ሞተርን በመጠቀም መኪናውን እንደሰራ የተናገረው ወጣቱ፣ የፈጠራ ሥራዎች እየተጠናከረ መምጣት የውጭ ምንዛሬን ከማስቀረት ባለፈ ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር እነደሚያስችልም አክሏል። በ8ኛው የከተሞች ፎረም ላይ በፈጠራ የተሰሩ መኪኖች ለእይታ እንዳልቀረቡ ያስታወሰው ወጣት አጃዬ፣ ዘንድሮ ለ9ኛ ጊዜ በተካሄደው የከተሞች ፎረም ላይ የተለያዩ መኪኖች ቀርበው መመልከቱን ተናግሯል። የፈጠራ ሥራዎች እያደጉ መምጣት ሥራ ፈጣሪዎችን በማነቃቃት ሀገራዊ አድገትን ለማፋጠን የራሱ ጠቀሜታ እንዳለውም ጠቁሟል። ፎረሙ ከተሞች ያላቸውን ሀብትና የሥራ ፈጠራ ውጤት እንዲያስተዋውቁ እድል መፍጠሩን የተናገሩት ደግሞ የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪው አቶ ዳዊት አብርሃም ናቸው። በአካባቢው በስፋት የሚመረተውን የሙዝ ምርት ወደ ዱቄት፣ ገንፎ፣ ኬክና ሌሎች ጣፋጭ ምግቦች እንዲሁም ኮባውን ወደ ቃጫነት ቀይሮ የሚሰራ ማሽን ሰርተው ፎረሙ ላይ ለእይታ ማቅረባቸውን ጠቅሰዋል። ከዚህ በፊት ከእንሰት ውጤት ይገኝ የነበረውን ቃጫ በአሁኑ ወቅት ከሙዝ እያመረቱ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ዳዊት፣ ፎረሙ ይሄንና አዳዲስ ፈጠራዎችን ከማቅረብ ባለፈ ሥራ ፈጣሪዎችን እርስ በእርስ ያስተዋወቀ መሆኑን ተናግረዋል። የከተሞች ፎረም "የዘመኑ ከተሞች ለኢትዮጵያ ብልጽግና" በሚል መሪ ሀሳብ ከየካቲት 9 እስከ 15 ቀን 2016 ዓ.ም በርካታ ከተሞች በተሳተፉበት በወላይታ ሶዶ ከተማ መካሄዱ የሚታወስ ነው።
አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ለሲዳማ ክልል የደህንነት ካሜራዎች ድጋፍ አደረገ
Feb 24, 2024 419
አዲስ አበባ፤ የካቲት 16/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ለሲዳማ ክልል የፀጥታ ተቋማትን ለማጠናከር የሚያገለግሉ የደህንነት ካሜራዎች ድጋፍ አደረገ፡፡ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ አቅምን የተላበሱት የደህንነት ካሜራዎቹ ግምታዊ ዋጋቸው 25 ሚሊዮን ብር መሆኑን የኢንስቲትዩቱ መረጃ ያመለክታል። ካሜራዎቹ የሐዋሳ ከተማን እንዲሁም የክልሉን ፖሊስ አሰራር በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማዘመን የዜጎችን ደህንነት ለማስጠበቅ ጉልህ ሚና እንደሚኖራቸው በርክክቡ ወቅት ተጠቅሷል፡፡ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ይታገሱ ደሳለኝ ለሲዳማ ክልል የሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ አለማየሁ ጢሞቲዎስ ካሜራዎቹን እና ተያያዥ የቴክኖሎጂ ቁሳቁሶችን አስረክበዋል። በርክክቡ ወቅትም አቶ አለማየሁ ጢሞቲዎስ ባስተላለፉት መልዕክት ኢንስቲትዩቱ ለክልሉ መንግሥት ላደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ የተረከቧቸው ቴክኖሎጂዎች ክልሉን ለማዘመን በሚደረገው ጥረት ላይ የሚኖራቸው ሚና ጉልህ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡