ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ስታርታፖች ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬት ገንቢ ሚና ይኖራቸዋል - ሚኒስቴሩ
Dec 29, 2025 117
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ ስታርታፖች የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነትንና እኩልነትን በማረጋገጥ ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬት ገንቢ ሚና እንደሚኖራቸው የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ገለጸ፡፡ ሚኒስቴሩ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ውጤቶችና በ2030 ስትራቴጂ የትኩረት መስኮች ላይ ከጋዜጠኞች ለቀረበለት ጥያቄ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉቀን ቀሬ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት መሰረት ጥሏል፡፡ የስትራቴጂው ስኬት የዲጂታል ኢኮኖሚ ልማትን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ቁልፍ መሳሪያ ሆኖ ያገለግላል ብለዋል፡፡ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ስታርታፖች የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነትና እኩልነትን በማረጋገጥ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ እና ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬት ገንቢ ሚና እንደሚኖራቸው ገልጸዋል፡፡ ስትራቴጂው አሁን ላሉት ስታርታፖች መሰረት መጣሉንም ነው ጨምረው የተናገሩት። ስታርታፖቹ የነገዋን የበለጸገች ኢትዮጵያ እውን ማድረግ የሚያስችሉ በዲጂታል የበቃ የሰው ኃይል ማፍራታቸውን ገልጸዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ 5 ሚሊየን ኮደርስ ስልጠና ሚሊዮነኖች ስታርታፖችን ለመፍጠር ግብዓት የሚሆኑበት አስቻይ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የተገበረችው የስታርታፕ አዋጅ ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንትን እንደሚስብ የጠቀሱት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ኢትዮጵያን የአፍሪካ የኢኖቬሽን ማዕከል ማድረግ ያስችላል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በርካታ ስታርታፖችን በማፍራት የአገልግሎት ተደራሽነትና ጥራትን ለማሳደግ እንደሚሰራም አስታውቀዋል፡፡ ስታርታፖች በሁሉም የሀገሪቱ ክፍሎች ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ፣ ጥራትና ፍጥነትን በማሻሻል ሁሉን አሳታፊ ለውጥ እንዲያስመዘግቡ ይጠበቃል ነው ያሉት፡፡ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉቀን ቀሬ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የምንገነባት ኢትዮጵያ በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘች እንድትሆን ማስቻል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ሀገራዊ ማንነትና እሴትን መሰረት ያደረገ አካታች የዲጂታል ኢኮኖሚ መሰረተ ልማት ግንባታን ማሳለጥ ያስችላል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ቅድሚያ ለሚሰጣቸው ዘርፎች ቴክኖሎጂን እንደ ግብዓት የመጠቀም ባህልን ማሳደግ የሚያስችል መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የሳይበር ደህንነትን በማጠናከር የዳታ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ያስችላል -ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)
Dec 29, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ታኅሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የሳይበር ደህንነትን በማጠናከር የዳታ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ውጤቶችና በ2030 ስትራቴጂ የትኩረት መስኮች ላይ ከጋዜጠኞች ለቀረበለት ጥያቄ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ከዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በፊት የዲጂታል ክፍያ ሥነ ምህዳር አልተፈጠረም አልያም በጅምር ላይ ነበር፡፡ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የክፍያ ሥርዓቱን በማዘመን በኢኮኖሚ ስርዓቱ ላይ ጉልህ ሚና ተጫውቷል ብለዋል፡፡ በግብይት ሥርዓቱ ቀልጣፋና ግልጽነት ያለው የዲጂታል ክፍያ ሥርዓትን በመጠቀም በዲጂታል ኢኮኖሚ ውጤት መለኪያዎች ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል፡፡ ይህም ለገንዘብ ህትመት የሚወጣውን የሀብት ብክነት በማስቀረት የዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት ወደፊት እንዲራመድ አድርጓል ብለዋል፡፡ በአጠቃላይ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ፖሊሲና ስትራቴጂዎችን በማውጣት፣ የኢንተርኔት ተደራሽነትና ትስስርን በማጠናከር የዲጂታል መሰረተ ልማትን በማሳለጥ ውጤታማ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የዲጂታል ኢኮኖሚ ሽግግርን ለመፍጠር የዲጂታል ክህሎት የታጠቀ ዜጋ መፍጠር ወሳኝ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፤ ባለፉት ዓመታት የመንግሥት ተቋማት በዲጂታል ክህሎት ልማት ሰፊ ሥራ መስራታቸውን ጠቁመዋል፡፡ በዚህም የዲጂታል ክህሎትና ግንዛቤን ለማሳደግ በ2016 ዓ.ም የ5 ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ስልጠና በመጀመር 2 ነጥብ 8 ሚሊየን ዜጎችን በመመዝገብ 1 ነጥብ 8 ሚሊየን ዜጎችን ዓለም አቀፍ ሰርተፊኬት እንዲያገኙ ማድረግ ተችሏል ብለዋል፡፡ ዓለም አቀፍ ሰርተፊኬቱን ያገኙ ዜጎች እውቀትና ክህሎታቸውን በመሸጥ አልያም ስታርት አፖችን በመፍጠር ለሀገር የዲጂታል ኢኮኖሚ እድገት ገንቢ ሚና እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ካለፈው የአምስት ዓመት ስትራቴጂ በጎ ልምዶችን በመውሰድ የተቀረጸ መሆኑን ያነሱት ሚኒስትሩ፤ የሳይበር ደህንነትን በማጠናከር የዳታ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ያስችላል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ዘመናዊ የዲጂታል ኢኮኖሚ ስርዓትን ለማንበር የዳታ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቶ የሚሰራበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በስትራቴጂው ዘመናዊ የዲጂታል ኢኮኖሚ በመገንባት የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ከግሉ ዘርፍና ዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በትብብር እንደሚሰራም አረጋገጠዋል፡፡
የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ስራዎች እየተከናወኑ ነው
Dec 29, 2025 182
ቴፒ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምርና ብዜት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል አስታወቀ። ማዕከሉ በሸካ ዞን ለመጀመሪያ ጊዜ በአርሶ አደሮች ያላመደውን "መልካም" የተሰኘ የማሽላ ዝርያ ለተለያዩ ባለ ድርሻ አካላት አስጎብኝቷል። የአርሶ አደሩን ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሰብል ምርምርና ብዜት ላይ በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን የማዕከሉ ዳይሬክተር ደረጀ ቱሉ(ዶ/ር) ገልጸዋል። በዚህም በሸካ ዞን የኪ ወረዳ ለመጀመሪያ ጊዜ የለማው "መልካም" የተሰኘ የማሽላ ዝርያ ምርታማነትን የሚያሳድግ ጥሩ የምርምር ውጤት መሆኑን ተናግረዋል። የምርምር ማዕከሉ የማሽላ ዝርያን ከማሻሻል በተጓዳኝ ሌሎች የሰብል ምርምርና ብዜት ላይ በመስራት የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ጥረት እያገዘ መሆኑን ገልጸዋል። የማዕከሉ ሰብል ምርምር ሥራ ሂደት አስተባባሪና ተመራማሪ ሸሀሚል አሎ፤ "መልካም" የተሰኘው የማሽላ ዝርያ በሔክታር እስከ 45 ኩንታል ምርት የሚገኝበት መሆኑን አንስተው ድርቅና በሽታን መቋቋም የሚችል መሆኑን ተናግረዋል። የሸካ ዞን ግብርና፣ ደን አካባቢ ጥበቃና ኅብረት ሥራ መምሪያ የሰብል ግብርና ባለሞያ አለሚቱ ካሳ፤ የተላመደው የማሽላ ዝርያ ከአካባቢው ሥነ ምህዳር ጋር ተሰማሚና ምርታማነቱም የተረጋገጠ በመሆኑ አርሶ አደሮች በስፋት እንዲጠቀሙት ይደረጋል ብለዋል። "መልካም" የተሰኘ የማሽላ ዘር በማሳቸው ያለሙት አርሶ አደር ታምራት እረና አዲሱ ዝርያ ከቀደመው የአካባቢ ዝርያ በፍጥነት ለምርት እንደሚደርስ ተናግረዋል። በሦስት ወር ምርት የሚሰጠው ይህን ዝርያን በቀጣይ በስፋት ለማምረት ማቀዳቸውን አክለዋል። በአርሶ አደር ታምራት ማሳ የለማውን የማሽላ ሰብል በማየት ዘር ተቀብሎ ለማልማት መወሰናቸውን የተናገሩት ደግሞ ሌላው የአካባቢው አርሶ አደር ጉዲሳ ቶልቻ ናቸው። የምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ አሁን የተመለከቱት ማሽላ እና ያገኙት ልምድን ለመተግበር ማቀዳቸውን ገልጸዋል፡፡ የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል በብሔራዊ ደረጃ ቅመማቅመምን ከማስተባበር ባሻገር ስንዴን ጨምሮ ሌሎች ለአካባቢው ተስማሚ የሰብል አይነቶች ላይ ምርምር በማድረግ የብዜትና ማስፋፊያ ሥራ እያከናወነ ነው።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ውጤታማነት ቁልፍ ሚና ይጫወታል
Dec 29, 2025 123
አዲስ አበባ፤ ታኅሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ውጤታማነት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት የፌዴራል መንግሥት ግዥና ንብረት አስተዳደር ባለሥልጣን ገለጸ። የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር መሰረት መስቀሌ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የመንግስትን የግዥ አሰራር ግልጽነት ለማስፈን የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት (e-GP) ተግባራዊ መደረጉን ገልጸዋል። በዚህም በ2018 በጀት ዓመት ሁሉም የፌዴራልና የመንግስት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚፈጽሙት ግዥ በኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት እንዲፈጸም እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓቱም የሀገር ውስጥና የውጭ ተጫራቾች እኩልና ግልጽ የመጫረቻ ዕድል የሚያገኙበትን ፍትሕዊ አሰራር እያሰፈነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓቱ አማካኝነት ከዕቅድ እስከ ግዥ የሚከናወኑ ሥራዎችን በግልጽ የተጠያቂነት የአሰራር ሥርዓት እንዲመራ በማስቻል ትልቅ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል። የመንግስት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትን ውጤታማነት ለማስጠበቅም ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር አስፈላጊ የሆኑ ሰነዶችን የማስተሳሰር ሥራ መሰራቱን ገልጸዋል። አቅራቢዎችም በግዥ ምዝገባ ወቅት የንግድ ፈቃድ፣ የግብር መለያ ቁጥርና የተጨማሪ ዕሴት ታክስ ምዝገባ ማረጋገጫቸውን በቀጥታ በዲጂታል ሥርዓት የሚያቀርቡበት አሰራር መሆኑንም አንስተዋል። በተሳሳተ ማንነት የመንግስት ግዥ እንዳይፈጸም ለማስቻልም ከብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ጋር በመተባበር ደረጃውን የጠበቀ ወጥ አሰራር ለመዘርጋት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም የፌዴራል መንግሥት ግዥና ንብረት አስተዳደር ባለሥልጣን ዘመናዊ የግዥ የአሰራር ሥርዓትን በመዘርጋት ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ውጤታማነት የድርሻውን እንደተወጣ አብራርተዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂም የመንግስትን የግዥ ሥርዓት ውጤታማነት ለማሻሻል ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል። በቀጣይም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መነሻነት ከፌዴራልና ከሁሉም ክልሎች ጋር በመተባበር የግዥ ሥርዓቱን ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሮኒክ ሥርዓት ለማስፈጸም ይሰራል ብለዋል።
የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የቴክኖሎጂ ክህሎት እና ተወዳዳሪነትን አሳድጓል
Dec 29, 2025 66
ሻሸመኔ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ያገኙት የቴክኖሎጂ እውቀት በዘርፉ ያላቸውን ክህሎትና ተወዳዳሪነት እንዳሳደገው የሻሸመኔ ከተማ የኮደርስ ሰልጣኞች ገለጹ። የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ 5 ሚሊዮን ዜጎች የቴክኖሎጂ ክህሎታቸውን በማዳበር ተጠቃሚ እንዲሆኑ ታቅዶ እየተሰጠ ነው፡፡ በሻሻመኔ ከተማ ስልጠናውን የወሰዱ ሰልጣኞች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርግ እውቀትና ክህሎት እንዳገኙ ተናግረዋል። መንግስት በነጻ ያመቻቸውን የስልጠና ዕድል ተጠቅመው በተለያዩ የቴክኖሎጂ ዘርፎች ሰልጥነው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን የተናገሩት አስተያየት ሰጪዎች፣ ስልጠናው የቴክኖሎጂ ክህሎታቸውን በማሳደግ በተሰማሩበት መስክ ተወዳዳሪነታቸውን ማሳደጉን ገልጸዋል። ስልጠናው ብዙዎች በተጨማሪ የገቢ ምንጭ ላይ ተሰማርተው ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያስችል መሆኑን የገለጸችው ወጣት መስከረም ደንደና ናት። በስልጠናው ያገኘችው እውቀት በየትኛውም አካባቢ ሄዳ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለመሆንና የራሷን ሥራ ለመፍጠርም እንደሚያስችላት ተናግራለች። በሁለት የቴክኖሎጂ ዘርፎች የሚሰጠውን ስልጠና በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት እንዳገኙና ቀሪዎቹን ስልጠናዎች እየተከታተሉ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ አቶ ሳፊ ከድር ናቸው። የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ዘመኑን የዋጀ የቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት በመያዝ ተወዳዳሪነታቸውን ማሳደጉን ገልጸው፣ ስልጠናው ተጨማሪ የሥራ ዕድል ለመፍጠር የሚያስችል ነው ብለዋል። በአራት የቴክኖሎጂ ዘርፎች የሚሰጠውን ስልጠና በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን የተናገሩት አቶ አብዮ ጀማል በበኩላቸው፣ ስልጠናው የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን እንዳሳደገው ተናግረዋል። ያገኙት እውቀት ራሳቸውን ከዓለም ጋር ለማስተዋወቅ፣ ቴክኖሎጂን በተሻለ ለመጠቀምና ቀልጣፋ አገልግሎት ለማግኘት እያገዛቸው መሆኑንም ተናግረዋል። በግል ከፍሎ ለመሰልጠን ቢታሰብ ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቀውን ስልጠና መንግስት በነጻ በማቅረቡ ያመሰገኑት አቶ አብዮ፣ ዜጎች በተለይ ወጣቶች ከዘመኑ ጋር ለመራመድ ዕድሉን ሊጠቀሙበት ይገባል ብለዋል። በሻሸመኔ ከተማ ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የከተማ አስተዳደሩ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ አብድሮ ፋይሳ ናቸው። በስልጠናው የመንግስት ሠራተኞች፣ ወጣቶችና ፍላጎቱ ያላቸው ሁሉ እየተሳተፉ መሆናቸውን ጠቁመው እስካሁን ድረስ ከ8 ሺህ በላይ ዜጎች ስልጠና ወስደው ማጠናቀቃቸውን ገልጸዋል። ስልጠናውን የወሰዱ የመንግስት ሠራተኞችም የቴክኖሎጂ ክህሎታቸውን በማሳደግ በስራቸው ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን አስረድተዋል።
በአሮሚያ ክልል በዲጂታል ቴክኖሎጂ አገልግሎት አሰጣጥን ማቀላጠፍ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Dec 27, 2025 145
አዲስ አበባ ፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡- በአሮሚያ ክልል በዲጂታል ቴክኖሎጂ የመረጃ አያያዝና የአገልግሎት አሰጣጥን ይበልጥ ቀልጣፋ ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ገለጸ። በክልሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ለብልፅግና ፓርቲ የአሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የበለፀገ "ሞሳጅ " የተሰኘ መተግበሪያ ዛሬ ተመርቆ ስራ ጀምሯል፡፡ የባለስልጣኑ ሀላፊ አቶ መኮንን በየነ እንዳመለከቱት፤ በክልሉ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ለማፋጠን በኢትዮ ቴሌኮም አማካኝነት የሞባይል ኔትዎርክ ሽፋን በገጠር ቀበሌዎች ተደራሽ ተደርጓል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የከተሞችን ዘመናዊነት ለማሳደግ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው የዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራ የከተሞችን አገልግሎት አሰጣጥ ለማዘመን መሠረት ጥሏል ዛሬ የተመረቀው መተግበሪያ የፓርቲውን የውስጥ አሰራርና አስተዳደርን የሚያዘምንና ለሌሎች የመንግስት መስሪያ ቤቶች አርአያ በመሆን እድገትን ለማፋጠን እንደሚያግዝ አንስተዋል። የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማስፋፋት የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥና መረጃዎችን ዲጂታላይዝድ በማድረግ ውጤታማ ተግባር መከናወኑን ጠቅሰው፤ ዘርፉን የማጠናከሩ ተግባር መቀጠሉንም ተናግረዋል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍና የአቅም ግንባታ ሀላፊ አቶ ነመራ ቡሊ እንደገለጹት፤ የበለፀገው መተግበሪያ ፓርቲው የዲጂታል ቴክኖሎጂ አሰራርን በመከተል ራሱን በማዘመን ሕዝቡ ጋር ለመድረሰ ታስቦ የተዘጋጀ እና የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትልሞችን የሚደግፍ ነው። የፓርቲውን አባላትና ሌሎችንም መረጃዎች ለመያዝ፤ ስርዓት ያለው የዳታ ሲስተም ለመዘርጋት፣ የእቅድና የግምገማ ስርዓትና የመዋቅርና የስራ አፈጻጸም የሚገመገምበት ዓይነተኛ መሳሪያ ነው ብለዋል። በክልሉ የዲጂታል 2025 ትግበራ በሁሉም የልማት ዘርፎች አመርቂ ውጤት ማምጣቱንም አቶ ነመራ አስታውሰዋል። የዲጂታል መሰረተ ልማትን የማሟላትና የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ላይ የእውቀትና ክህሎት ማሳደጊያ ስራን በማጠናከር ዲጂታል 2030ን እውን ለማድረግ ርብርብ እንደሚደረግም ገልጸዋል።
ለትውልዱ ምቹ ሀገር የማስረከብ ጉዞ በሁሉም መስክ በስኬታማነት ቀጥሏል- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Dec 27, 2025 167
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በአረንጓዴ የብልጽግና ጉዞ ለትውልዱ ምቹ ሀገር የማስረከብ ጉዟችን በሁሉም መስክ በስኬታማነት ቀጥሏል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የኢትዮጵያ ብክለት ቀናሽ እንቅስቃሴ (ግሪን ሞቢሊቲ) 2025 ዐውደ ርዕይና መድረክ ዛሬ በይፋ ከፍተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት በአረንጓዴ የብልጽግና ጉዞ ለትውልዱ ምቹ ሀገር የማስረከብ ጉዞ በሁሉም መስክ በስኬታማነት መቀጠሉን ገልጸዋል። አውደ ርዕዩ እና መድረኩ ኢትዮጵያ ተፈጥሮን ለመካስና ብክለት ቀናሽ ኢኮኖሚ ለመገንባት የጀመረችው ታሪካዊ ጉዞ ማሳያ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት ላይ የተመሠረተ ስኬታማ የብልፅግና ጉዞ ላይ ትገኛለች - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ የትራንስፖርት ዘርፍ ታሪካዊ ሽግግር ላይ ትገኛለች - ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ(ዶ/ር) ዐውደ ርዕዩ አዳዲስ የአረንጓዴ ትራንስፖርት ቴክኖሎጂዎች ለዕይታ የሚቀርቡበት ከመሆኑም በላይ፤ በመንግሥት፣ በባለሀብቶችና በኅብረተሰቡ መካከል የጋራ ግንዛቤና ትብብር የሚፈጥር መድረክ እንደሆነም ተናግረዋል። ከአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነት ለመውጣት እንደ አረንጓዴ ዐሻራና የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ማስፋፋት ያሉ ውጤታማ የአረንጓዴ ልማት ርምጃዎች በመንግስት እየተወሰዱ እንደሚገኝ አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በዘመናዊና አረንጓዴ ትራንስፖርት ዓለምን ለመምራት ዝግጁ ናት ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ታዳሽ ኃይልን ከዘመናዊ ትራንስፖርት ጋር በማቀናጀትና የካርበን ልቀትን በመቀነስ ኢትዮጵያን በአፍሪካ የአረንጓዴ ኢንዱስትሪ ጉዞ ቀዳሚ እያደረግናት እንገኛለን ሲሉ ገልጸዋል። ለትውልዱ በሁሉም መስክ ምቹ ሀገርን ለማስረከብም የአረንጓዴ ብልጽግና ጉዞ ተጠናክሮ ቀጥሏል ነው ያሉት። ለራዕዩ መሳካት የመንግሥት ብቻ ሳይሆን የእያንዳንዱ ግለሰብና ተቋም ዘመኑን የመዋጀት የባህልና የአስተሳሰብ ለውጥ እንዲሁም ቁርጠኝነት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። እኛ ስለ አረንጓዴ ዕድገት የምንጨነቀው ስለ መጪው ትውልድ ስለምንጨነቅ ነው፤ መንግሥት ለዚህ ዓላማ ስኬታማነት የመሪነት ሚናውን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት ላይ የተመሠረተ ስኬታማ የብልፅግና ጉዞ ላይ ትገኛለች - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Dec 27, 2025 131
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት ላይ የተመሠረተ ስኬታማ የብልፅግና ጉዞ ላይ እንደምትገኝ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሁለተኛውን ሀገራዊ “የብክለት ቀናሽ እንቅስቃሴ(ግሪን ሞቢሊቲ) 2025” ሳምንት ዛሬ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በይፋ ከፍተዋል። በመክፈቻ ንግግራቸውም የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ዋነኛ መሠረቱ አረንጓዴ ልማት መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ያስመዘገበችውን ድል በአረንጓዴ ትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ዘርፍ ለመድገም እየሰራች መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህም ለበካይ ጋዝ የካርቦን ልቀት ቅነሳ እና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኢኮኖሚ ሥርዓት ለመገንባት በቁርጠኝነት እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም፤ የሰው ልጅ ከተፈጥሮ ጋር የነበረውን ቅራኔ መፍታት የሚችለው ብክለትን በሚቀንሱ ቴክኖሎጂዎች ጉዞውን ሲመራ ብቻ መሆኑን አስረድተዋል። ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ውይይቶች ከንግግር ባለፈ ወደ ተግባር መሸጋገር እንዳለባቸውም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ውጤትና ተግባር ተኮር የመፍትሔ አካሄድን እየተከተለች መሆኗን በማንሳት፤ ብክለት ቀናሽ የአረንጓዴ እንቅስቃሴና የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች መስፋፋት የዚሁ ተግባራዊ ምላሽ ዋነኛው ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። በአረንጓዴ ዐሻራ፣ ወንዞችን ከብክለት በማፅዳት፣ የፌስታል ምርቶችን አጠቃቀም በመገደብና በታዳሽ ኃይል የሚንቀሳቀሱ ተሽከርካሪዎችን በማስፋፋት ረገድ ትልቅ ሥራ መከናወኑን ጠቅሰዋል። ታዳሽ ኃይል የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን ከንጹሕ የኢነርጂ መሠረተ ልማት በተለይ ከሃይድሮ ኤሌክትሪክ፣ ከፀሐይና ከነፋስ ኃይል ጋር ማቀናጀት፣ የካርቦን መጠንንና የኃይል ወጪዎችን ለመቀነስ ወሳኝ መሆኑንም ጠቁመዋል። በዘላቂ ትራንስፖርት ላይ ያተኮሩ ውጥኖች የካርቦን ልቀትን ለመግታት ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያን በአፍሪካ በአረንጓዴ ኢንዱስትሪያላዊነት አፈጻጸም ግንባር ቀደም እንደሚያደርጋት አንስተዋል። አውደ ርዕዩ የኢትዮጵያን ብክለት ቀናሽ አብዮት የሚያበረታቱ ቴክኖሎጂዎች ማሳያ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም ፖሊሲ አውጪዎች፣ ባለሀብቶችና ዜጎች በጋራ እየተገነባ ስላለው ዘላቂና ዘመናዊ የትራንስፖርት አገልግሎት ግንዛቤና ልምድ እንዲኖራቸው ያስችላል ብለዋል። የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ በአረንጓዴ ልማት ላይ የተመሠረተ እንዲሆን መንግሥት አበክሮ እየሠራ መሆኑን በማንሳት፤ ለስኬቱ ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል ተግባራዊ ምላሽ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርበዋል። መንግሥት ለዚህ ዓላማ ስኬታማነት ሁሌም የመሪነት ሚናውን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራ የከተሞችን አገልግሎት አሰጣጥ ለማዘመን መሠረት ጥሏል
Dec 27, 2025 114
ጎንደር፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡- የዲጂታል ኢትዮጵያ ትግብራ የከተሞችን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማዘመን መሠረት መጣሉን የጎንደር ከተማ አስተዳደር የስማርት ሲቲ ዳይሬክተር ይልቃል ሙሉአለም (ዶ/ር) ገለጹ። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 መጠናቀቅን ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በቅርቡ ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የጎንደር ከተማ አስተዳደር የስማርት ሲቲ ዳይሬክተር ይልቃል ሙሉአለም (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ ከተሞችን በቴክኖሎጂ በማደራጀት ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል። ስማርት ሲቲን በመፍጠር የከተሞችን ምጣኔ ሀብታዊና ማህበራዊ አገልግሎቶች እንዲቀላጠፉ የራሱን ሚና እንደሚጫወትም ነው የገለጹት፡፡ በተለይም ዲጂታል ፋይናንስን ለማቀላጠፍና ወንጀልን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት አጋዥ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ዲጂታል ኢትዮጵያ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ለማሳካትና ወጥ የሆነ የመረጃ አያያዝን በማጠናከር ለሀገራዊ እድገት ጉልህ ድርሻ እያበረከተ መሆኑንም ነው የገለጹት። የአርተፊሻል ኢንተለጀንስና የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መጀመር ዲጂታል ኢትዮጵያን ስኬታማ ለማድረግ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆንም አስረድተዋል። የመንግስት አገልግሎት በቴክኖሎጂ ታግዞ መሰጠቱ ተጠያቂነትንና ግልጸኝነትን በማስፈን ሲስተዋሉ የነበሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡ እንደ ይልቃል (ዶ/ር) ገለጻ፤ ኢትዮጵያ እስከ 2030 የሚዘልቅ የዲጂታል ስትራቴጂ መንደፏ ዓለም አቀፍ ተቀባይነትና ተወዳዳሪነቷን የሚያሳድግ ነው። ከአማራ ክልል ከተሞች መካከል ጎንደር በስማርት ሲቲ ቴክኖሎጂ የመጀመሪያና ፈር ቀዳጅ ተግባራትን እያከናወነች መሆኑን የገለጹት ዳይሬክተሩ፣ ይህም የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ዘርፉን ለማነቃቃት ያስችላል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በቅርቡ በይፋ ማስጀመራቸው የሚታወስ ነው፡፡
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የከተሞችን ዘመናዊነት ለማሳደግ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው
Dec 27, 2025 93
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡- የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በቴክኖሎጂ የዘመኑ ከተሞችን ለመፍጠርና የዜጎችን የአኗኗር ሁኔታ ለማሻሻል ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል ዕድል መፍጠር እንዲሁም በዜጎችና ተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት የስትራቴጂው ቁልፍ ትልሞች መሆናቸውን መግለጻቸው ይታወቃል። እነዚህን ትልሞች ለማሳካት የሕዝብ ዲጂታል መሠረተ ልማትን ማስፋፋት ቁልፍ ተግባር መሆኑን ጠቅሰው ይህም ቴክኖሎጂን ሰው ተኮር በማድረግ የዜጎችን የዕለት ተዕለት ኑሮ ለማሻሻል ትልቅ አቅም ይፈጥራል ብለዋል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የመደመር መንግሥት ከተሞች የፈጠራ፣ የቴክኖሎጂ እና የብልጽግና ማሳያ እንዲሆኑ እየሰራ ነው። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ከተሞችን ስሉጥ (ስማርት ሲቲ) ለማድረግ የሚያስችል ጠንካራ መሠረት መጣሉን ተናግረዋል፡፡ ይህም ከተሞች ከዕቅድ ዝግጅት ጀምሮ በዲጂታል መንገድ እንዲመሩ በማስቻል እና የአገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። በዚህም ለነዋሪዎች ምቹ ከተማ፣ የኤሌክትሮኒክ ግብይት እንዲሁም ለዜጎች የተቀላጠፈ አገልግሎት መስጠት የተቻለበት እንደነበረ አንስተዋል። በዚህም የሚታይ ውጤት እና ለከተሞች እድገት ትልቅ መሰረት ጥሎ በስኬት መጠናቀቁን ገልፀዋል። አዲሱ 2030 ዲጂታል ስትራቴጂ ከተሞች ከስማርት ከተማነት ባለፈ በቴክኖሎጂ የዘመኑ እንዲሆኑ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። አዲሱ የከተማ ልማት ፖሊሲም ከስትራቴጂው ጋር በቀጥታ የሚዛመድ ሲሆን፤ የኃይል አጠቃቀምን፣ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴን፣ የአገልግሎት አሰጣጥን እንዲሁም በሰዎች እንቅስቃሴ ውስጥ ብልህነትን የሚያሰርጽ መሆኑን አስረድተዋል። ዲጂታላይዜሽን በዜጎችና በመንግሥት እንዲሁም በአገልግሎት ሰጭና ተቀባይ መካከል መተማመንን የሚፈጥር መሆኑንም ነው የገለጹት፡፡ የመረጃ ደኅንነትን በማረጋገጥ መረጃዎችን ለሀገር ዕድገት የመጠቀም ልምድ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየሰፋ መምጣቱንም በአብነት ጠቅሰዋል። የመደመር መንግሥት ከተሞች የፈጠራ፣ የቴክኖሎጂ እና የብልጽግና ማሳያ እንዲሆኑ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑንና ዲጂታላይዜሽን ለዚህ ስኬት ዋነኛው የመስፈንጠሪያ አቅም መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
የኢንተርፕረነርሽፕ ልማት ፖሊሲ ከዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ጋር ተጣጣሚ በሆነ መልኩ የተዘጋጀ ነው
Dec 26, 2025 127
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 17/2018(ኢዜአ)፦የኢንተርፕረነርሽፕ ልማት ፖሊሲ ከዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ጋር ተጣጣሚ በሆነ መልኩ መዘጋጀቱን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፥ የኢንተርፕረነርሽፕ ልማት ረቂቅ ፖሊሲን አስመልክቶ ከዲጂታል ካውንስል አባላት ጋር በበይነ መረብ ውይይት አካሂደዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፥ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በሁሉም መስክ የሥራ ፈጠራ ባህልን በማስረጽ ቀጣይነት ያለው እና ፈጣን ዕድገትን ዕውን ለማድረግ ኢንተርፕረነርሽፕ ቁልፍ መሳሪያ ነው ብለዋል። ፖሊሲው በዋናነት ሁሉን አቀፍ እና አካታች ሀገራዊ የኢንተርፕረነርሽፕ ንቅናቄን በማቀጣጠል በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ጋር ተጣጣሚ በሆነ መልኩ የዲጂታል ሥራ ፈጠራንና ተወዳዳሪነትን የሚያበረታታና የሚደግፍ መሆኑን አመልክተዋል። የፖሊሲ ማዕቀፉ ችግር ፈች ማህበረሰብን ለመገንባት፣ የፈጠራ ባህልን ለማጎልበት፣ እሴትን ለመጨመር እንዲሁም ምቹ ስነምህዳርን ለመገንባት የሚያስችል የኢኮኖሚ ዕድገት ማዕቀፍ እንደሆነም ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ የኢትዮጵያን የኢንተርፕረነርሽፕ ስነ-ምህዳርና የስራ ፈጠራ ውጥኖችን አቅጣጫ በመስጠት የመምራት ቁልፍ ሚና አለው ነው ያሉት። በተለይ የኢንተርፕረነርሽፕ ስነ-ምህዳሩን ሊያሻሽሉ የሚችሉ የጋራ አመለካከቶችን፣ እምነቶችንንና ባህሪያትን ለማጎልበት በእጅጉ እንደሚያግዝ አብራርተዋል። በውይይቱ የልማት ፖሊሲው የታለመለትን ውጤት ማምጣት እንዲችል በፖሊሲው ትግበራ ወቅት የሚታዩ ጠንካራ እና ደካማ ጎኖችን በመለየት በየደረጃው ወጥና ጠንካራ የክትትል ስርዓት መዘርጋት እንደሚገባ ከዲጂታል ካውንስሉ ጋር መግባባት መፈጠሩን ገልጸዋል። በኢንተርፕረነርሽፕ ልማት ረቂቅ ፖሊሲ ላይ ጥልቅ ውይይት በማድረግ እና ግብዓቶችን በመጨመር የልማት ፖሊሲ ሰነዱ ወደ ሚኒስትሮች ምክር ቤት ተልኮ እንዲፀድቅ መወሰኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል።
የዲላ ከተማ ማዘጋጃ ቤታዊ ዲጂታል አገልግሎት ተገልጋዮች ፈጣን መስተንግዶ እንዲያገኙ አስችሏል
Dec 26, 2025 96
ዲላ፤ ታህሳስ 17/2018(ኢዜአ)፦የዲላ ከተማ ማዘጋጃቤታዊ አገልግሎት ዲጂታል መደረጉን ተከትሎ ፈጣን አገልግሎት እያገኙ መሆናቸውን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። አገልግሎቱን በማዘመን ከወረቀት ንክኪ ነጻ መደረጉ ለተጠቃሚዎች ፈጣን አገልግሎት ለመስጠትና ገቢን ለማሳደግ ከማስቻሉ ባለፈ የተቋሙን የመፈጸም አቅም ማሳደጉም ተመላክቷል። የከተማው ነዋሪዎች ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ዲጂታል መደረጉን ተከትሎ ፈጣንና የተሻለ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን አንስተዋል። ከዚህ ቀደም በማዘጋጃ ቤቱ አንድ ጉዳይ ለማስጨረስ በቀጠሮ የሚያጠፉት ጊዜና ጉልበትን ከማስቀረቱ ባለፈ ለብልሹ አሰራር የነበረባቸውን ተጋላጭነትም በእጅጉ መቀነሱን ተናግረዋል። ኢዜአ ካነጋገራቸው ነዋሪዎች መካከል አቶ ከበደ ወራሳ፤ በወረቀት ያለውን የካዳስተር ይዞታቸውን ወደ ዲጂታል ለመቀየር እንደመጡ ገልጸው፣ በአንድ ቀን ጉዳያቸውን ጨርሰው በመመለሳቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል። ይህም ከዚህ ቀደም አንድ ጉዳይ ለማስጨረስ ለበርካታ ቀናት ሲደርስባቸው የነበረውን እንግልትና ምልልስ በማስቀረት የጊዜና የገንዝብ ብክነትን እንዳስቀረላቸው አንስተዋል። በመንደራቸው ከረጅም ጊዜ በፊት ተለክቶ ያልተሰራ መንገድ በኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴ ላይ ጫና በመፍጠሩ ይህን የህዝብ ቅሬታ ይዘው እንደመጡ የገለጹት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ ክፍሌ ሎላ ናቸው። በማዘጋጃ ቤቱ በተጀመረው የፊት ለፊት አገልግሎት የልማት ጥያቄያቸው ለሚመለከተው የሥራ ሃላፊ ቀርቦ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተስፋ የሚሰጥ ምላሽ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። በማዘጋጃ ቤቱ የተጀመረው ዘመናዊ አገልግሎት ከዚህ ቀደም አንድ ጉዳይ ለማስጨረስ ከቢሮ ቢሮ የቀጠሮ ምልልስ ነበረው፤ በዚህም ጊዜና ጉልበት ይባክን ነበር ብለዋል። ማዘጋጃ ቤቱ አገልግሎቱን ማዘመኑ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ ከማስቻሉ ባለፈ ለብልሹ አሰራር የነበራቸውን ተጋላጭነት በእጅጉ መቀነሱን አስረድተዋል። የመኖሪያ ቤት ጥያቄያቸውን ይዘው ለረጅም ጊዜ ምላሽ ሳያገኙ ተቸግረው መቆየታቸውን የተናገሩት ወይዘሮ ሃያሌ ሠራዊት የተባሉ ነዋሪ በበኩላቸው፣ ማዘጋጃ ቤቱ አገልግሎቱን ማዘመኑን ተከትሎ ጥያቄያቸው ሰሚ አግኝቶ በሚመለከተው የሥራ ክፍል እየታየ መሆኑን ገልጸዋል። ዲጂታል አገልግሎቱ በማዘጋጃ ቤቱ ከዚህ በፊት የሚነሳውን የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግር የቀረፈ ነው ብለዋል። ተቋሙ ከተያዘው በጀት ዓመት ጀምሮ አሰራሩን በማዘመን የግንባታ፣ መሬት አስተዳደር፣ የማዘጋጃ ቤታዊ ገቢን ጨምሮ 71 አገልግሎቶችን ዲጂታል ማድረጉን ያነሱት ደግሞ የዲላ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤት ምክትል ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሃብታሙ ተፈሪ ናቸው። በዚህም አገልግሎቶች ከወረቀት ንክኪ ነጻ በሆነ መንገድ እየተሰጡ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ ይህም ፈጣን አገልግሎት በመስጠት የተገልጋዩን ማህበረሰብ ጊዜና ጉልበት ለመቆጠብ ማስቻሉን ጠቁመዋል። በቴክኖሎጂ ታግዞ የሚሰራው ሥራ የህብረተሰቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች ከመፍታት ባለፈ የተቋሙን የእለት ገቢና የመፈጸም አቅም አሳድጎታል ብለዋል።
ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር በተጓዳኝ ለዲጂታል ልማት ስኬት የበኩሉን እየተወጣ ነው
Dec 26, 2025 125
ጂንካ፤ ታህሳስ 17/2018(ኢዜአ)፦የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ስራው በተጓዳኝ ለዲጂታል ልማት ስኬት የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን የዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ሽግግር እና የማህበረሰብ አገልግሎት ገለጸ። የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከእውቀት ማእከልነቱ ባለፈ ለባህልና ለተፈጥሮ ሃብት ልማት ልዩ ትኩረት በመስጠት አካባቢያዊ እውቀትን ከዘመናዊ ሳይንስ ጋር በማቀናጀት ለማህበረሰብ እመርታዊ ለውጥና ተጠቃሚነት እየሰራ ይገኛል። ዩኒቨርሲቲው በተለይም በማህበረሰብ ተኮር ምርምሮች እና በቴክኖሎጂ ሽግግር ዙሪያ ትኩረት አድርጎ ከሚሰራባቸው ዋና ዋና ዘርፎች መካከል በግብርና እና የእንስሳት ሃብት፣ የቱሪዝም ልማትና የባህል ጥበቃ፣ የማህበረሰብ አገልግሎት የፈጠራ ስራዎች፣ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ (ICT) እና ሌሎችም ይገኙበታል። በመሆኑም በዚህ ሰፊ የስራ እንቅስቃሴ ውስጥ እስካሁን የተከናወኑ ተግባራትንና የቀጣይ አቅጣጫዎች በተመለከተ ኢዜአ በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ሽግግር እና የማህበረሰብ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር የሆኑትን ካሳሁን የማነህ (ዶ/ር) አነጋግሯል። የዲጂታል ኢትዮጵያን እቅድ በማሳካት ሂደት የ5 ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና አንዱ መሆኑን አንስተው በዚህ ጥረት ውስጥ ዩኒቨርሲቲው የድርሻውን እየተወጣ ይገኛል ብለዋል። የኮደርስ ስልጠና ከወሰዱት የዩኒቨርሲቲው መምህራን፣ ተማሪዎችና ሰራተኞች መካከል 1 ሺህ 73ቱ ሰርተፍኬት መውሰዳቸውን ገልጸዋል። አሁን ላይ በዩኒቨርሲቲው የኤሌክትሮኒክ ትምህርት ክፍል አስተባባሪነት 1 ሺህ 879 የሚሆኑ መምህራን፣ተማሪዎችና የአስተዳደር ሰራተኞች የኮደርስ ስልጠና እየተከታተሉ መሆኑን ጠቁመው በቀጣይ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችን በማስፋትና በማበልፀግ በዘርፉ የካበተ ዕውቀት ያለው ዜጋ ለማፍራት የበኩሉን ይወጣል ብለዋል። በዩኒቨርሲቲው የኮደርስ ስልጠና ከወሰዱት መካከል መምህር አስመራ አምዴ፤ የኮደርስ ስልጠና ዘመኑ የሚጠይቀው የዲጂታል ቴክኖሎጂ እውቀት መሆኑን ገልጸው እድሉን በአግባቡ መጠቀም ይገባል ብለዋል። በዚህ ዘመን የሰው ሰራሽ አስተውሎትና ሌሎችም ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የተግባርና የፈጠራ አቅምን ማሳደግ አስፈላጊ ስለመሆኑም አንስተዋል። በዩኒቨርሲቲው የአይ ሲቲ ጥገና ባለሙያ ግዛቸው ገንዶሌ፤ የኮደርስ ስልጠና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ብቁ ባለሙያ ሆኖ ለመገኘት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮ ኮደርስ ከተዘጋጁ 4 ኮርሶች 3ቱን በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት መውሰዳቸውን ገልፀው፥በቀጣይም ሙሉ በሙሉ ለማጠናቀቅ ማቀዳቸውንም ተናግረዋል ። ኮርሱ የያዛቸው ይዘቶች እጅግ ጠቃሚና የዲጂታል ክህሎትን የሚያሰፋ በመሆኑ ሌሎችም የነፃ ስልጠና እድሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ መክረዋል።
በዲጂታል ልማት ዘርፍ የተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት በአገልግሎት አሰጣጥና በሰዎች የኑሮ ዘይቤ ላይ እመርታዊ ለውጥ አምጥቷል - ምሁራን
Dec 26, 2025 88
ሐረማያ፤ ታህሳስ 17/2018(ኢዜአ)፦ በዲጂታል ልማት ዘርፍ ባለፉት አምስት ዓመታት የተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት በአገልግሎት አሰጣጥና በሰዎች የኑሮ ዘይቤ ላይ እመርታዊ ለውጥ ማምጣቱን በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የሚሰሩ ምሁራን ገለጹ። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ላለፉት አምስት ዓመታት ሲተገበር ቆይቶ በቅርቡ በስኬት መጠናቀቁ ይታወቃል። በዚህ የትግበራ ሂደት በቴሌኮም እና ኢንተርኔት መሠረተ ልማት፤ በዲጂታል ክፍያ እና የፋይናንስ ዘርፍ፤ በዲጂታል መታወቂያ እና በተለያዩ የመንግስት አገልግሎቶች ላይ የሚታዩ ለውጦችና ተጨባጭ ውጤቶች ተመዝግበዋል። በመሆኑም የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በስኬት መጠናቀቁን ተከትሎ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በይፋ ተጀምሯል። ከዲጂታል ልማት ትግበራ እና የቀጣዩን እቅድ በተመለከተ ኢዜአ ያነጋገራቸው በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የሚሰሩ ምሁራን በዲጂታል ልማት ዘርፍ ባለፉት አምስት ዓመታት የተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት በአገልግሎት አሰጣጥና በሰዎች የኑሮ ዘይቤ ላይ እመርታዊ ለውጥ ማምጣቱን ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል ሃላፊና መምህር ሚልኬሳ ደጀኔ፤ በዲጂታል ዘርፍ ኢትዮጵያ እመርታዊ ለውጥና ማንሰራራት ላይ መሆኗን ብዙ ማሳያዎች እንዳሉ ተናግረዋል። በቴሌኮም እና የኢንተርኔት መሠረተ ልማት፣ በፋይናንስ፣ በተለያዩ የመንግስት አገልግሎቶችና ሌሎችም በዲጂታል አገልግሎት የሚገለጡ ማሳያዎች አሉ ብለዋል። ከዚህ ስኬት በመነሳትም የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ቁልፍ ትልሞች ስኬታማ እንደሚሆኑ ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የኮምፒቲንግና ኢንፎርማቲክ ኮሌጅ ምክትል ዲንና መምህር አፈንዲ አብዲ፤ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በኢትዮ ቴሌኮም መሰረተ ልማት ማስፋፋት ጋር በተያያዘ የ4ጂ እና 5ጂ ኔትወርክ ዝርጋታ ለዘርፉ ልማት ፅኑ መሰረት ማኖሩን ገልጸዋል። ከዚህ በመነሳት በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ተደራሽነትን የማስፋት፣ ለዜጎች እኩል እድል መፍጠር እና በዜጎችና በተቋማት መካከል መተማመንን የመፍጠር ቁልፍ ተግባር በቀላሉ የሚሳካ መሆኑን አንስተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በቅርቡ ይፋ የተደረገው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ያለፈውን ስኬት በማስቀጠል በዘርፉ ልማት የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ማድረግ የሚያስችል ነው።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት ለመስጠት አስችሏል
Dec 26, 2025 80
ሚዛን አማን፤ ታህሳስ 17/2018 (ኢዜአ):- የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት ለመስጠት ማስቻሉ ተመላከተ። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በተያዘለት ግብ መሠረት ውጤታማ በሆነ መንገድ መጠናቀቁን፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ይፋ ባደረጉበት ወቅት መግለጻቸው ይታወሳል። በጉዳዩ ዙሪያ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የሚገኙ ሁለት ተቋማት ኃላፊዎች እንዳሉት ባለፉት አምስት ዓመታት በሀገራችን የተዋወቀው የዲጂታል አገልግሎት ውጤታማ ነው። በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሚዛን ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ አቶ በረከት ትጉ የዲጂታል ሥርዓት ተቋማትን ብሎም ተገልጋይ ዜጎችን ከእንግልት የሚታደግ ዘመኑ የደረሰበት ቴክኖሎጂ ውጤት ነው ብለዋል። ከ5 ዓመታት ወዲህ በዲጂታል ዘርፍ በርካታ ለውጦች መመዝገባቸውን ገልጸው በዚህም አብዛኛው የባንኩ አገልግሎት ዲጂታላይዝ እንዲሆን ማስቻሉን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ዓለም በዘርፉ ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ የዋጀ ሥራ አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው በ2025 የታየው መልካም ተሞክሮ ለ2030ው ዲጂታል ኢትዮጵያ ግብ ትልቅ አቅም አንደሚሆን ጠቁመዋል። አገልግሎቱን ይበልጥ በማስፋፋት ተደራሽነቱ ላይ መሥራትና በቴክኖሎጂ ዘርፍ የዓለም ገበያን የሚመጥን ሥራ ሠርቶ የሀገር ሉዓላዊነትን ማስጠበቅ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ምክትል ሥራ አስፈጻሚ አቶ አህመዲን አወል በበኩላቸው መንግሥት የሕዝብ ተጠቃሚነትን በሚያረጋግጥ መልኩ ቴክኖሎጂን እያስፋፋ ነው። ለአብነትም በቅርቡ ወደ ተግባር ገብቶ በርካታ የአገልግሎት ለውጦች እየተመዘገቡበት ያለው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከወረቀት ነጻና ዘመናዊ በመሆኑ ድካምን የሚቀንስ ሆኗል ብለዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ማድረግ ወቅቱ የሚጠይው መሆኑን ጠቅሰው በዚህ እሳቤ ማዕከሉ በክልሉ በዲጂታል መንገድ የሚሰጡ አገልግሎቶችን ለማሳደግ እየሠራ እንደሚገኝ አመልክተዋል። የዲጂታል ሥርዓት መስፋፋት የዜጎችን የጊዜ፣ የጉልበትና የገንዘብ ብክነትን የመታደግ ፋይዳ የጎላ ሲሆን ይህም በክልሉ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከ35 በላይ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ እየሰጠ ባለው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እየተረጋገጠ ነው ብለዋል።
የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና የቴክኖሎጂ እውቀታችንን በማዳበር ሥራችንን አቀላጥፏል -ሰልጣኞች
Dec 26, 2025 88
ወልቂጤ ፤ ታህሳስ 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና በቴክኖሎጂ ያላቸውን እውቀት በማሳደግ ሥራቸውን ለማቀላጠፍና ውጤታማ ለማድረግ እያገዛቸው መሆኑን በወልቂጤ ከተማ ሰልጣኞች ተናገሩ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በተጀመረው የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ስልጠናው ለ5 ሚሊዮን ዜጎች ተደራሽ እንዲሆን ግብ ተይዟል። ስልጠናው ዜጎች የተክኖሎጂ እውቀታቸውን ለማሳደግና በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎትን ለማስፋት ያለውን ጠቀሜታ ጉልህ እንደሆነ ታምኖበት ወደተግባር ከተገባ ሦስተኛ ዓመቱን ይዟል። የኢትዮ-ኮደርስ ስልጥና እየተሰጠባቸው ካሉ አካባቢዎች በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ እንዱ ሲሆን የስልጠናው ተሳታፊዎችም የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማሳደግ ሥራቸውን ለማሳለጥ እያገዛቸው መሆኑን ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት መካከል ወጣት ሄኖክ ወልደጊዮርጊስ እንደገለፀው፣ በአራት የተለያዩ ዘርፎች የቀሰመው የቴክኖሎጂ ክህሎትና እውቀት ብቁና ተወዳዳሪ ባለሙያ እንዲሆን እያስቻለው ነው። በተከታታይ የወሰደው ስልጠና እየሰራ ባለበት የመንግስት ተቋም ሥራውን ቴክኖሎጂን ተጠቅሞ ለማከናወን ከማስቻሉ ባለፈ በእረፍት ጊዜው የግል ሥራ ጭምር በመስራት ተጠቃሚ እንዳደረገው ተናግሯል። ሌላው ሰልጣኝ ወጣት ወልደተንሳይ ወልደአምላክ በበኩሉ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ያገኘውን ነጻ የስልጠና ዕድል በመጠቀም የተለያዩ አገልግሎት የሚሠጡ ሶፍትዌሮችን አበልጽጎ ተጠቃሚ መሆኑን ገልጿል፡፡ በንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩት ወይዘሮ ሮዛ አግዛ በበኩላቸው የወሰዱት ስልጠና የቴክኖሎጂ ክህሎትና ዕውቀታቸውን በማሳደግ በንግድ ሥራቸው ውጤታማ እያደረጋቸው መምጣቱን ተናግረዋል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በጉራጌ ዞን ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ 58 ሺህ ዜጎች ስልጠናውን እንደወሰዱ የገለፁት ደግሞ የጉራጌ ዞን ሳይንስና ቴክኖሎጂ መምሪያ ሃላፊ አቶ ደምስ ገብሬ ናቸው። በዞኑ በተያዘው በጀት ዓመት 24 ሺህ ዜጎችን ለማሰልጠን ታቅዶ እስካሁን ድረስ ለ36 ሺህ ዜጎች ስልጠና መሰጠቱን የገለጹት ሃላፊው፣ "ከእነዚህ ውስጥ 28 ሺህ ዜጎች ስልጠናውን ጨርሰው የምስክር ወረቀት ወስደዋል" ብለዋል። በኢትዮ ኮደርስ ስልጥና ብዛት ያላቸው ሰልጣኞች የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማዳበር አዳዲስ የቴክኖሎጂ መተግበሪያዎችን ማልማት እየቻሉ መሆኑንም ተናግረዋል። በስልጠናው የሚሳተፉ ዜጎች ቀጥር እያደገ መምጣት ለዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራ የሚያበረክተው ፋይዳ የላቀ እንደሆነ ጠቁመዋል፡፡ በቀጣይ ስልጠናውን በሁሉም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ሙሉ በሙሉ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም አቶ ደምስ አመላክተዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በዲጂታል ክህሎትና ኢኮኖሚ ግንባታ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነውበታል
Dec 26, 2025 104
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 17/2018(ኢዜአ)፦ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለዲጂታል ክህሎትና ኢኮኖሚ ግንባታ መሰረት የሆኑ ውጤታማ ተግባራት እንደተከናወኑበት የቴክኖሎጂ ዘርፍ ምሁራን ገለፁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ መሳካቱን መግለጻቸው ይታወቃል። በተለይም በሕዝብ መገልገያ ዲጂታል መሠረተ ልማቶች ዝርጋታ ውጤታማ ሥራ መከናወኑን አንስተው፤ ኢትዮጵያ ወሳኝ በሚባል ደረጃ ከጥሬ ገንዘብ ግብይት ወደ ዲጂታል የፋይናንስ ስርዓት መሸጋገሯን ጠቅሰዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ተደራሽነትን የማስፋት፣ እኩል እድልን የማመቻቸት፣ በተቋማትና ህዝብ መካከል መተማመንን የመፍጠር ቁልፍ ትልሞች እንዳሉት አብራርተዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን እንዳሉት፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ መሰረት የጣለና አገልግሎቶችን በማዘመን ተደራሽነትን ማሳደግ ያስቻለ ነው። በዩኒቨርሲቲው የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስና ሮቦቲክስ ልህቀት ማዕከል ኃላፊ ሀቢብ መሀመድ(ዶ/ር)፣ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የኢንተርኔት ፍጥነትን በማሻሻልና የሞባይልና ኢንተርኔት ተጠቃሚዎችን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ በመጨመር ውጤታማነቱን በተግባር ማሳየቱን ገልጸዋል። ስትራቴጂው ለዲጂታል ኢኮኖሚ መሰረት የጣለና በርካታ የመንግስት አገልግሎቶች አሰጣጥን በማዘመን የአገልግሎት ተደራሽነትና ፍጥነት ማሳደጉን ተናግረዋል። የፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ቢሮክራሲን ለመቀነስ ሚና እንዳለው አንስተው፤ እንደ አምስት ሚሊየን ኮደርስ ያሉ የዲጂታል አካታችነትና ክህሎትን የሚያሳድጉ መርሃ ግብሮች መተግበራቸውንም አስረድተዋል። የስትራቴጂው ትግበራ አካታች የፋይናንስ ሥርዓትን በመገንባት፣ የዲጂታል ክፍያና የሞባይል ፋይናንስ አገልግሎቶችን በስፋት ተደራሽ ማድረጉን ገልጸዋል። በተጨማሪም፣ የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚው ውስጥ ያለውን ተሳትፎ ከማሳደግ ባለፈ፣ የሳይበር ደህንነትን ለማረጋገጥ የተከናወኑ ስራዎች ስትራቴጂው የተቀመጡለትን ግቦች ማሳካቱን ማሳያ መሆናቸውን አስረድተዋል። በዩኒቨርሲቲው የሶፍትዌር ኢንጂነሪንግ ትምህርት ክፍል ኃላፊ ለምለም ካሳ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 መሰረተ ልማቶችን ከማሳለጥ፣ አገልግሎቶችን ከማዘመን አኳያ ውጤት የተመዘገበበት መሆኑን ተናግረዋል። ምሁራኑ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የኢትዮጵያን ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ማፋጠን፣ መሰረተ ልማቶችን ማጠናከር፣ ፈጠራን ማበልፀግ፣ ለሀገር በቀል ዲጂታል ኢኮኖሚ የሚያስፈልጉ ተቋማት የመገንባት ራዕይን የሰነቀ መሆኑን ጠቅሰዋል። ስትራቴጂውን በውጤታማነት ለመተግበር በዲጂታል መሰረተ ልማትና ክህሎት ግንባታ እና የሳይበር ደህንነት ላይ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸውም ገልፀዋል።
ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በምርምር ያገኘውን የእንስሳት መኖ የሳር ዝርያ እያስፋፋ ነው
Dec 26, 2025 78
ሐረማያ፤ ታህሳስ 17/2018 (ኢዜአ)፡- ሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በምርምር ያገኘውን የእንስሳት መኖ የሳር ዝርያ እያስፋፋ መሆኑን አስታወቀ። የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ በተፈጥሮ ሃብት አያያዝና አካባቢ ሳይንስ ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ዳርጎ ከበደ ለኢዜአ እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው “ላይም ግራስ” የተሰኘን የእንስሳት መኖ የሳር ዝርያ በምርምር አግኝቷል። በምርምር የተገኘውን የሳር ዝርያ በምስራቅ ሐረርጌ ዞንና ማያ ከተማ መስተዳድር በሚገኙ ሶስት ወረዳዎች እና አራት ቀበሌዎች በአርሶ አደር ግብርና ማሰልጠኛ ማዕከላትና በአርሶ አደር ማሳ ላይ እያስፋፋ መሆኑን ተናግረዋል። የሳር ዝርያው በአንድ ሽህ አባወራ አርሶ አደሮች ማሳ ላይ መስፋፋቱን አመልክተዋል። ቀደም ሲል በአካባቢው የነበሩት የሳር ዝርያዎች እርጥበትንና ሰፋፊ ቦታዎችን በከፍተኛ ሁኔታ የሚፈልጉና የሰብሎችን ንጥረ ነገርና ውሃ የሚሻሙ መሆኑን ጠቁመው “ላይም ግራስ” የተሰኘው የሳር ዝርያ ውርጭ፣ የዝናብ እጥረትና ድርቅን በመቋቋም በአነስተኛ መሬት ብዛት ያለው የሳር መኖ የሚያስገኝ መሆኑን አመልክተዋል። የሳር ዝርያው ከአንድ ወር እስከ አንድ ወር ተኩል ጊዜ ውስጥ ፈጥኖ የሚደርስ መሆኑንም ጠቁመው በተጠቀሱት ባህርያቱ በሐረርጌ አካባቢ የሚስተዋለውን የእንስሳት መኖ ችግር የሚቀርፍ መሆኑን ገልጸዋል። የሳር ዝርያው ለእንስሳት መኖነት ከእርጥብነት በተጨማሪ በድርቆሽነትም የሚያገለግል መሆኑን ጠቁመው በከብት እርባታና ማድለብ ስራ የተሰማሩ አካላትን ውጤታማ ያደርጋል ብለዋል፡፡ በተለይም የሳር ዝርያው በያዘው ንጥረ ነገር ከእንስሳት ሃብት የሚገኘውን የስጋ ምርታማነትን የሚጨምር መሆኑም በምርምሩ በተካሄደ የከብቶች ምገባ መረጋገጡን አመልክተዋል። እንዲሁም ዘሩን በማምረትና ለገበያ በማቅረብ በገቢ ምንጭነት በመጠቀም የተሻለ ጥቅም ማግኘት እንደሚቻል ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው የሳር ዝርያውን ወደ አርሶ አደሩ በማስፋፋት ከእንስሳት ዘርፍ የሚገኘውን ገቢ የማሳደግ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።
የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለዲጂታል ኢትዮጵያ ስኬታማነት ጉልህ አስተዋጽኦ አለው
Dec 25, 2025 126
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 16/2018 (ኢዜአ)፡-የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለዲጂታል ኢትዮጵያ ስኬታማነት ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተገለጸ። "ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለኢትዮጵያ ማንሰራራት" በሚል መሪ ሀሳብ ስለ ኢትዮጵያ የውይይት መድረክ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል በጉባ ወረዳ ታላቁ ህዳሴ ግድብ በሚገኝበት ሥፍራ ተካሂዷል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ መሠረት ኃይሌ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያን ብልጽግና በተግባር የሚያሳይ ፕሮጀክት ነው። የታላቁ ህዳሴ ግድብ የህዝቦች አብሮነት የተንጸባረቀበትና ለትውልድ የሚተላለፍ የታሪክ አሻራ መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም ለኢንዱስትሪ ምርታማነትና ለሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ እድገት ወሳኝ ነው ብለዋል። በተለይም ዲጂታላይዜሽንን እውን በማድረግ በሁሉም ዘርፎች ስኬታማ ስራዎች እንዲሰሩ ያለው አበርክቶ ከፍተኛ መሆኑንም ጠቁመዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ በበኩላቸው፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ የከፍታ መገለጫ ነው ብለዋል። ታላቁ የህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያውያን ኩራትና የትውልዱ ታላቅ ቅርስ መሆኑን አውስተው፤ ለቱሪዝም ልማት የማዋል ተግባር ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ነው ያስረዱት። ግድቡ ለቱሪዝም ዘርፉ ይዞ የመጣውን እድል አሟጦ ለመጠቀም በዘርፉ አዳዲስ የአሰራር ስርዓቶችን በመዘርጋት ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ በበኩላቸው፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ስኬት ተጨማሪ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ለማለም እድል የፈጠረ ነው ብለዋል። በተለይም ኢትዮጵያ ያላትን ሃብት ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባ በተግባር ያሳየና መሰረታዊ ተጠቃሚነትን ያረጋገጠ ስለመሆኑም አንስተዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽህፈት ቤት ዋና ስራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ታላቁ ህዳሴ ግድብ በሁሉም ኢትዮጵያውያን ዘንድ የይቻላል መንፈስን የፈጠረ ነው። በግድቡ ግንባታ የታየውን ህብረት በሌሎች ስራዎች ላይ እውን ለማድረግ ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ፖሊሲ ጥናት ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ፍቃዱ ጸጋ በሰጡት ማጠቃለያ፤ የታላቁ ህዳሴ ግድብ እውን መሆን የሃይል አቅርቦት እንዲያድግ እድል መፍጠሩን ጠቁመው፤ ይህም ለኢንዱስትሪ ምርታማነት፣ ለዲጂታል ኢትዮጵያ ስኬታማነትና ለሌሎች ዘርፎች ውጤታማነት ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አብራርተዋል። ግድቡ የኢትዮጵያን ማንሰራራት በተግባር በማሳየት ረገድ ትልቅ ምሳሌ መሆን መቻሉን ጠቅሰዋል።
ህንድ ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬታማነት ያላትን ሰፊ ተሞክሮ ታጋራለች
Dec 25, 2025 131
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 16/2018(ኢዜአ)፦ ህንድ ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬታማነት በዲጂታል የህዝብ አገልግሎት መሰረተ ልማት ያላትን ሰፊ ተሞክሮ ለማካፈል ዝግጁ መሆኗን በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ገለፁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ መሳካቱን መግለጻቸው ይታወቃል። በተለይም በሕዝብ መገልገያ ዲጂታል መሠረተ ልማቶች ዝርጋታ ውጤታማ ሥራ መከናወኑን አንስተው፤ ኢትዮጵያ ወሳኝ በሚባል ደረጃ ከጥሬ ገንዘብ ግብይት ወደ ዲጂታል የፋይናንስ ስርዓት መሸጋገሯን ጠቅሰዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ባለፉት አምስት ዓመታት የተከናወኑ ተግባራትን መሠረት በማድረግ መዘጋጀቱን ጠቅሰው፤ ተደራሽነትን ማስፋት፣ እኩል እድልን በማመቻቸትና በተቋማትና ህዝብ መካከል መተማመንን የመፍጠር ቁልፍ ትልሞች እንዳሉት አብራርተዋል። በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በሀገሪቱ የሚተገበሩ የዲጂታል ዕቅዶችን ለመወጠን መሰረት የተጣለበት ነው። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂም የ5ጂ ኔትወርክንና የፋይዳ መታወቂያን በመላው ሀገሪቱ ተደራሽ ማድረግ የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል። ይህም የባንክ አገልግሎትን በመላ ሀገሪቱ በማዳረስ የፋይናንስ አካታችነትን ለማረጋገጥና ዜጎች በሀገሪቱ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የነቃ ተሳትፎ ለማድረግ እንዲችሉ አስተዋፅኦ እንዳለው አንስተዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲን ይፋዊ የስራ ጉብኝት ተከትሎ የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ወደ ስትራቴጂክ አጋርነት ማደጉ የሀገራቱን ትብብር እንደሚያጠናክር ጠቅሰው፤ በጋራ ከሚሰራባቸው ዘርፎች አንዱ ዲጂታላይዜሽን መሆኑንም ገልፀዋል። ህንድ በዲጂታል መሰረተ ልማት ያላትን ተሞክሮ ለኢትዮጵያ በማጋራት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኗንም አብራርተዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ጠንካራ የዲጂታል መሰረተ ልማት በመዘርጋት ሀገሪቱን የሚለውጥ መሆኑን አንስተው ህንድ ኢትዮጵያ ለጀመረችው ስኬታማ ጉዞ የድርሻዋን እገዛ እንደምታደርግ አረጋግጠዋል።