ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ለኒውክሊየር ኃይል ጣቢያ ግንባታ የሚሆን ምቹ አካባቢን በጥናት የመለየት ሥራ ተጀምሯል
May 18, 2026 137
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ለኒውክሊየር ኃይል ጣቢያ ግንባታ ምቹ አካባቢን በጥናት የመለየት ሥራ እየተካሄደ መሆኑን የኢትዮጵያ ኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን አስታወቀ። ኮሚሽኑ ከዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ (IAEA) ጋር በመተባበር ያዘጋጀውና በኒውክሊየር ኃይል መገንቢያ ቦታ መስፈርቶችና ቅድመ ሁኔታዎች ላይ ትኩረት ያደረገ አውደ ጥናት እያካሄደ ይገኛል። ለአራት ቀናት በሚካሄደው በዚህ አውደ ጥናት ላይ ባለሙያዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት በመሳተፍ ላይ ናቸው። የኢትዮጵያ ኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ሽፈራው ተሊላ በወቅቱ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ በሁሉም መስክ ያሉ እድገቶችን ቀጣይነት ለማረጋገጥ አስተማማኝ እና ዘላቂ የኃይል አቅርቦት ወሳኝ ነው። በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ በየዓመቱ 40 ቴራ ዋት አወር (TWh) ኃይል እንደሚያስፈልግ የገለጹት ምክትል ኮሚሽነሩ፤ በዚህም በሚቀጥሉት አስር ዓመታት ውስጥ የኃይል ፍላጎቱ ወደ 77 ቴራ ዋት አወር ከፍ እንደሚል ጠቁመዋል። በሀገሪቱ የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት፣ የዲጂታል መሰረተ ልማት እንዲሁም የአገልግሎት ዘርፉ እያደገ መምጣት ከፍተኛ የኃይል አቅርቦት እንደሚጠይቅ ጠቅሰዋል፡፡ ይህንን የኃይል ፍላጎት በከፊል ከኒውክሊየር ኃይል ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ኮሚሽኑ ከኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ጋር በመተባበር የኒውክሊየር ኃይል ጣቢያ ለመገንባት የትኛው አካባቢ ምቹ እንደሆነ ለመለየት የሚያስችል ጥናት እያካሄደ መሆኑ ተገልጿል። በአሁኑ ወቅት የዳሰሳ ጥናቱ እየተጠናቀቀ መሆኑን የገለጹት አቶ ሽፈራው፤ በቀጣይ ይበልጥ ዝርዝር ጥናቶች ተደርገው ግንባታው የሚካሄድበት ትክክለኛ ቦታ መረጣ ይከናወናል ብለዋል። አሁን እየተካሄደ ያለው አውደ ጥናት ለቦታ መረጣው አስፈላጊ በሆኑ መስፈርቶችና አካሄዶች ላይ ጠቃሚ ግብዓት ለማግኘት እንደሚረዳም ጠቅሰዋል፡፡ በዘርፉ የሰው ኃይል አቅም ግንባታ እና አስፈላጊ የሕግ ማዕቀፎችን ሥራ ላይ ለማዋል የዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙም አክለዋል፡፡ በዓለም አቀፉ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ የኒውክሊየር ደህንነት ከፍተኛ ባለሙያ ሚካኤል ሳልሞን በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይልን ለእድገት ማቀላጠፊያ መሳሪያ ለማድረግ ህልም ሰንቃ ጉዞ መጀመሯ ትልቅ ውሳኔ ነው ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ግንባታ እቅድ እንዲሳካ ኤጀንሲው አስፈላጊውን የቴክኒክና የሙያ ድጋፍ ማድረጉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
የፖሊሲ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የራስን መረጃ በራስ አቅም መሰብሰብና መተንተን ወሳኝ ነው- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 18, 2026 119
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ የፖሊሲ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የራስን መረጃ በራስ አቅም መሰብሰብ እና መተንተን ወሳኝ ግብዓት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነጻነት'' በተሰኘውና ኢትዮጵያ በመረጃና በስታቲስቲክስ የሉዓላዊነት ጉዞ ያስመዘገበችውን ትልቅ ድል በተበሰረበት ሀገራዊ ጉባኤና ኤግዚቢሽን ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በዘርፉ የተመለከቱት እመርታ እጅግ አስደሳች ሆኖ እንዳገኙት ገልጸዋል። መረጃ የዚህ ዘመን ስትራቴጂካዊ ሀብት እና ጠንካራ ሀገረ መንግሥት የሚገነባበት ቁልፍ የሉዓላዊነት ምሰሶ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቁመዋል። የተዋሰ አሊያም በውጭ አካላት ላይ ጥገኛ የሆነ መረጃ ሀገራዊ መሻታችንን ማሳካት ስለማያስችል፤ የፖሊሲ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የራስን መረጃ በራስ አቅም መሰብሰብ እና መተንተን ወሳኝ ግብዓት እንደሆነ አስገንዝበዋል። ከሁሉም በላይ የመረጃ አሰባሰብና ትንተና ሥራ በሀገር ልጆች እውቀትና ክህሎት ሲከወን ማየት ታላቅ ሀገራዊ ኩራት መሆኑን በመልዕክታቸው አንስተዋል። በተጨማሪም የመረጃ ትኩረታችን በቁጥር በሚገለጹ ውጤቶች ላይ ብቻ ሳይሆን ሰው ተኮር በሆኑና በዜጎች ሕይወት በሚታዩ ተጨባጭ ለውጦችም ላይ መሆን እንዳለበትም ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሳስበዋል።
ኢትዮጵያ በሚቀጥሉት አስርት ዓመታት ለሚመዘገበው ዕድገት መሠረት የሚሆን የሉዓላዊ ዲጂታል መሠረተ ልማት እየገነባች ነው
May 18, 2026 107
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በሚቀጥሉት አስርት ዓመታት ለሚመዘገበው ዕድገት መሠረት የሚሆን የሉዓላዊ ዲጂታል መሠረተ ልማት እየገነባች መሆኑን የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) ገለጹ። ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው ሀገራዊ ጉባኤ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት በመካሄድ ላይ ነው። በመድረኩ ማብራሪያ የሰጡት የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) ኢትዮጵያ በሚቀጥሉት አስርት ዓመታት ለሚመዘገበው ዕድገት መሠረት የሚሆን የሉዓላዊ ዲጂታል መሠረተ ልማት እየገነባች ነው ብለዋል። እንደ ግብርና፣ ጤና፣ ፋይናንስ፣ ትምህርት እና ኢነርጂ ያሉ እያንዳንዱ ዘርፎች አሁን ላይ በሀገር በቀል የክላውድ ቴክኖሎጂ የሚቀነባበሩ፣ በሀገር ውስጥ የሚመሩ እና በኢትዮጵያ ቋንቋዎች መግባባት ለሚችለው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ግብዓት የሚሆኑ ተግባራዊ መረጃ ምንጮች ሆነዋል ነው ያሉት። የራሳችን መረጃ ከሌለን የኛ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ባዕድ ይሆናል፤ የራሳችን አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ከሌለን ደግሞ መረጃዎቻችን ይባክናሉ ሲሉም አብራርተዋል። "ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ይህንን ክፍተት ለመሙላት የተቀረጸ ብሔራዊ ስትራቴጂ ሲሆን፤ ይህም ሉዓላዊ የክላውድ ዳታ ሴንተርን፣ ብሔራዊ የዳታ ሌክ ሀውስን እንዲሁም በአማርኛ፣ በአፋን ኦሮሞ፣ በትግርኛ እና በሶማሊኛ ቋንቋዎች የሰለጠነ እና ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ ቁጥጥር ስር የሚመራ ሀገር በቀል ላርጅ ላንግዌጅ ሞዴልን መገንባትን ያካትታል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ ቀዳሚ እየሆኑ ያሉት ሀገራት መረጃቸውን ወደ ምርታማነትና ወደ አዲስ የኢኮኖሚ እሴት እየቀየሩ ያሉ ናቸው፤ ኢትዮጵያም አሁን ላይ ይህንኑ መሠረት እየገነባች ትገኛለች ብለዋል።
ኢትዮጵያ የጥላቻ ንግግርና የተዛቡ መረጃዎችን ለመከላከል የሚደረገውን ቀጣናዊ ጥረት በግንባር ቀደምነት ትደግፋለች
May 18, 2026 94
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በዲጂታል ትስስር መስፋፋትና በሰው ሰራሽ አስተውሎ (AI) የሚታገዙ የጥላቻ ንግግሮችና የተዛቡ መረጃዎችን ለመከላከል በሚደረገው ቀጣናዊ ጥረት ኢትዮጵያ በግንባር ቀደምነት ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኗን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፍጹም ግርማ ገለጹ። የምስራቅ አፍሪካ በይነ-መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የጥላቻ ንግግርንና ሀሰተኛ መረጃዎችን ለመከላከል ያዘጋጀው የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል። የአፍሪካ ህብረት ተወካዮች፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ የኢጋድ ከፍተኛ አመራሮች፣ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢንሳ)፣ የመከላከያ ሚኒስቴር፣ የመገናኛ ብዙኃን (ሚዲያ) እንዲሁም የሙያ ማህበራት ተወካዮች በመድረኩ ላይ ተገኝተዋል። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር ጄኔራል አቶ ፍጹም ግርማ እንደገለጹት፤ የዲጂታል መድረኮች መስፋፋትና የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ መራቀቅ የጥላቻ ንግግሮችና የተዛቡ መረጃዎች ስጋትን ይበልጥ አጠናክሮታል። ኢትዮጵያ ይህንን ስጋት ለመግታት አገራዊ እርምጃዎችን በግንባር ቀደምትነት መውሰዷን ጠቅሰው ፤ በተለይም በጥላቻ ንግግሮችና በሀሰት መረጃዎች ላይ ግልጽ የወንጀል ተጠያቂነትን የደነገገውን "የጥላቻ ንግግር እና የሀሰት መረጃ ስርጭትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የወጣውን አዋጅ" በምሳሌነት አንስተዋል። ሆኖም ግን አገር በቀል ጥረቶች ብቻቸውን በቂ እንዳልሆኑ ጠቁመው፤ የችግሩ ድንበር ተሻጋሪነት የጋራ ምላሽ የሚሻ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። ድንበር ተሻጋሪ ስጋቶችን በብቸኝነት መከላከል ስለማይቻል የመንግስታት ትብብር፣ ቀጣናዊ ተቋማት፣ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ያካተተ የተቀናጀና ባለብዙ ወገን ምላሽ እንደሚያስፈልግ አፅንዖት ሰጥተዋል፡፡ ኢጋድ ይህንን የጋራ የመረጃ ስነ-ምህዳርን የማፅዳትና የቀጣናውን ሰላምና ማህበራዊ ትስስር የመጠበቅ ተነሳሽነት መውሰዱ የሚደነቅ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከኢጋድ፣ ከአፍሪካ ህብረት፣ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅትና ከሌሎች አጋሮች ጋር በመሆን ስጋቶቹን ለመቆጣጠርና የቀጣናውን ሰላምና ብልፅግና ለማረጋገጥ ዝግጁ መሆኗን አረጋግጠዋል። የኢጋድ የግጭት ቅድመ-ማስጠንቀቂያና ምላሽ መስጫ ዳይሬክተር ካልሙስ ኦሞንጎ በበኩላቸው፤ መድረኩ የሚመለከታቸው አካላት መረጃዎችን በተቀናጀ ሁኔታ የሚለዋወጡበት፣ በጋራ ወቅታዊ ሁኔታዎችን የሚገመግሙበትና ተያያዥ አደጋዎችን አስቀድመው የሚለዩበት ተግባራዊ የሥራ ትስስር እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ይህም ማኅበረሰብን የሚከፋፍሉ መረጃዎች ከመሰራጨታቸው በፊት አስቀድሞ የመለየት እና ተገቢውን ሕጋዊና ሙያዊ ምላሽ የመስጠት ሂደትን ያቀናጃል ሲሉ አብራርተዋል። የኢጋድ ሰላምና ደህንነት ዘርፍ ዳይሬክተር ኮማንደር አበበ ሙሉነህ በበኩላቸው፤ የጥላቻ ንግግሮችና የተዛቡ መረጃዎች ድንበር ተሻጋሪ ስጋቶች ስለሆኑ የሁሉም አገራት ትብብር ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ በተለይ የመገናኛ ብዙኃን አካላት ግጭትን በመከላከል፣ እውነታን በማረጋገጥና ኃላፊነትን በመጠየቅ ረገድ ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑን አስታውቀዋል። በመሆኑም ጋዜጠኞች መረጃዎችን በአግባቡ እንዲያረጋግጡ፣ አርታኢያን የዜና አቀራረብ ስልታቸውን በጥንቃቄ እንዲመርጡ እንዲሁም ተቋማት ደግሞ ግልጽና ወቅታዊ መረጃዎችን ለሚዲያ አካላት እንዲሰጡ ጥሪ አቅርበዋል። መድረኩ ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ይሆናል።
የኢትዮጵያ ዲጂታል ሉዓላዊነት ከርዕይነት ባለፈ በተግባር ላይ ውሏል
May 18, 2026 80
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዲጂታል ሉዓላዊነት አሁን ላይ ከርዕይነት ባለፈ በተግባር ላይ የዋለ መሠረተ ልማት ሆኗል ሲሉ የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የዕቅድ ክትትልና ግምገማ ዲጂታላይዜሽን ዘርፍ ኃላፊ ዘሪሁን ከበደ ገለጹ። ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው ሀገራዊ ጉባኤ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት በመካሄድ ላይ ነው። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የዕቅድ ክትትልና ግምገማ ዲጂታላይዜሽን ዘርፍ ኃላፊ ዘሪሁን ከበደ እንደገለፁት፤ የኢትዮጵያ ዲጂታል ሉዓላዊነት አሁን ላይ ከርዕይነት ባለፈ በተግባር ላይ የዋለ መሠረተ ልማት ሆኗል። ይህ የዲጂታል ዕቅድ ክትትልና ግምገማ ሥርዓት እያንዳንዱን ብሔራዊ አመላካች፣ የሪፎርም ፕሮግራም እና የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶችን ቁልፍ የአፈጻጸም አመላካቾች በአንድ በተረጋገጠ ብሔራዊ መድረክ ላይ እንዲመሩ የሚያደርግ ነው ብለዋል። በዚህ ሥርዓት ውስጥ የሚገኘው አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በፌዴራልና በክልል ተቋማት ውስጥ ከሚገኙና ከጸደቁ ብሔራዊ መረጃዎች ላይ በመነሳት፣ የመረጃ ምንጮችን በመጥቀስ አሁናዊ ምላሾችን እንደሚሰጥ አመልክተዋል። በመሆኑም የተበታተነ መረጃ እና የዘገየ ውሳኔ አሰጣጥ የነበረው የአመራር ፈተና አሁን ላይ ታሪክ ሆኗል ሲሉም ተናግረዋል። ሥርዓቱ ተገንብቶ ተጠናቋል፤ የአመራርና የክትትል ማዕቀፉም ሥራ ላይ ውሏል፤ የተመዘገቡት ስኬቶችም ተጨባጭ እንደሆኑም ነው የገለጹት። ይህም ለእያንዳንዱ ቁጥር አንድ የታመነ የመረጃ ምንጭ መኖርን፣ ሙሉ ተጠያቂነትንና የኦዲት ዐሻራን ከማረጋገጡም በላይ፣ አመራሩ ጊዜ ያለፈባቸው ሪፖርቶች ላይ ሳይሆን በወቅታዊ መረጃዎች ላይ ተመስርቶ ውሳኔ እንዲያስተላልፍ ማስቻሉን ተናግረዋል። ቀጣዩ ምዕራፍ የእያንዳንዱ ተቋም ኃላፊነት ይሆናል፤ ይህም ከዚህ አንድ ወጥ ብሔራዊ ሥርዓት ጋር መገናኘት፣ ሥርዓቱን ተግባራዊ ማድረግ እና በዛም አማካኝነት መምራትን እንደሚያጠቃልል ገልጸዋል።
የመረጃ ሥርዓት ሪፎርሙ ፖሊሲዎች በማስረጃ ላይ እንዲመሠረቱና ተቋማዊ ተጠያቂነት እንዲሰፍን አድርጓል
May 18, 2026 66
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ የመረጃ ሥርዓት ሪፎርሙ ፖሊሲዎች በማስረጃ ላይ እንዲመሠረቱና ተቋማዊ ተጠያቂነት እንዲሰፍን ማድረጉን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ በረከት ፍስሃጽዮን አመለከቱ። ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው ሀገራዊ ጉባኤ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት እየተካሄደ ይገኛል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ በረከት ፍስሃጽዮን በጉባኤው ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸው፤ የኢትዮጵያ የልማት አስተዳደር ሪፎርም ሀገሪቱ የምታቅድበትን፣ ክትትል የምታደርግበትንና ውጤት የምታስመዘግብበትን አካሄድ መሠረታዊ በሆነ መልኩ እየቀየረው እንደሚገኝ ተናግረዋል። ላለፉት በርካታ ዓመታት የተቀናጀ ሥርዓት አለመኖር፣ በእቅድና በፋይናንስ መካከል የነበረው ደካማ ትስስር እንዲሁም በሂደት ላይ ብቻ ያተኮሩ ሪፖርቶች ሀገራዊ ተጠያቂነትን አዳክመውት እንደነበር አስታውሰዋል። ይህ ሪፎርም እነዚህን መዋቅራዊ ክፍተቶች በቀጥታ በመቅረፍ፤ ኢትዮጵያን ከመረጃ ማመንጨት ባለፈ መረጃን ጥቅም ላይ ለማዋል እንዲሁም የአፈጻጸም ተግባራትን በመረጃ ሳይደገፍ ከመመዝገብ ይልቅ ለዜጎች የመጡ ተጨባጭ ለውጦችን ለመለካት ወደሚያስችል ወሳኝ ምዕራፍ ማሸጋገሩን አመልክተዋል። ዛሬ ላይ ከ113 በላይ የመንግሥት ተቋማት በአንድ ዕቅድ እና በአንድ ሪፖርት መርህ ላይ በተመሰረተ እንዲሁም ሙሉ በሙሉ በዲጂታል በተደገፈ የአፈጻጸም ክትትልና ግምገማ ሥርዓት ስር እንደሚሰሩም ነው ሚኒስትር ዴኤታው የጠቆሙት። ሀገሪቱ ደረጃቸውን የጠበቁ ብሔራዊ የኢኮኖሚ ሂሳቦችን፣ የተናበበ የክልሎች አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርትን፣ ጠንካራ የህዝብ ኢንቨስትመን ማዕቀፍን እና ወቅታዊ አፈጻጸም ክትትልን ተግባራዊ በማድረግ የ10 ዓመቱን የልማት ዕቅድ ለማሳካት የሚያስችላትን ተቋማዊ ሉዓላዊነት እየገነባች እንደምትገኝም ገልጸዋል። ይህም እያንዳንዱ የወጣ ገንዘብ ተጠያቂነት ያለው፣ እያንዳንዱ ፖሊሲ በማስረጃ ላይ የተደገፈ እና ለእያንዳንዱ ዜጋ ዋጋ ያለው መሆኑን ያረጋገጠ ነው ብለዋል ሚኒስትር ዴኤታው።
በዩኒቨርሲቲው የሲቪል ሰርቪስ አሰራርና የሰው ሃይል ልማትን የሚያጠናክር ውጤታማ የምርምር ሥራዎችን እየተከናወኑ ነው
May 18, 2026 41
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የሲቪል ሰርቪስ አሰራርና የሰው ሃይል ልማትን የሚያጠናክር ውጤታማ የምርምር ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የዩንቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ንጉስ ታደሰ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ 11ኛውን ዓመታዊ የምርምር ጉባኤ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ማካሄድ ጀምሯል። ጉባኤው ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ሲሆን በተለያዩ ምሁራን የጥናትና ምርምር ሥራዎች ቀርበው ውይይት እንደሚደረግባቸው ተመላክቷል። በዚሁ ጊዜ የዩንቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ንጉስ ታደሰ (ዶ/ር)፤ በተለያዩ መስኮች ብቁና የሰለጠነ የሰው ሃይል ማፍራት የሚያስችሉ የጥናትና ምርምር ውጤቶች እየፈለቁ እንደሚገኙ ገልጸዋል። የሰለጠነ የሰው ሃይል የማፍራትና የተቋማትን አቅም የሚያጠናክር የምርምር ሥራዎችም የሲቪል ሰርቪስ አሰራርና የሰው ሃይል በማፍራት እየደገፈ መሆኑን ተናግረዋል። 11ኛው ዓመታዊ የምርምር ጉባኤም የሲቪል ሰርቪሱን ውጤታማነት ለማሻሻል ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ አንስተዋል። በሁነቱ የሲቪል ሰርቪስ ሥርዓቱን የሚያዘምኑ የምርምር ውጤቶች ቀርበው ምክክር እንደሚደረግባቸው አስረድተዋል። በጉባኤው የሚገኙ ውጤቶችና ባለድርሻ አካላት የሚሰጧቸው ግብዓቶች ተቀምረው ጥቅም ላይ እንዲውሉ እንደሚደረግ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ብሔራዊ ስታቲስቲክስን የልማት ማዕከል በማድረግ የመረጃ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ እየሠራች ነው
May 18, 2026 33
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ስታቲስቲክስን የልማት ማዕከል በማድረግ የመረጃ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ እየሠራች እንደምትገኝ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የኢኮኖሚ ስታቲስቲክስ ዘርፍ ኃላፊ አብዱልአዚዝ ሸፋ ገለጹ። ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው ሀገራዊ ጉባኤ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት እየተካሄደ ይገኛል። የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የኢኮኖሚ ስታቲስቲክስ ዘርፍ ኃላፊ አብዱልአዚዝ ሸፋ በጉባኤው ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም ኢትዮጵያ ብሔራዊ ስታቲስቲክስን የልማት ማዕከል በማድረግ የመረጃ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት እየሠራች መሆኑን አስገንዝበዋል። በዚህም መሠረት፣ ተቋሙ ቀድሞ የነበረውን የወረቀት ላይ አሠራር በማስቀረት ሙሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል የመረጃ አሰባሰብ መሸጋገሩን ጠቁመዋል። ይህ ሽግግር የግብርና ቆጠራን እንዲሁም የስነ-ሕዝብና ጤና ጥናትን ዘመናዊ ለማድረግ ያስቻለ ሲሆን፣ በዘርፉ ላይ ከፍተኛ ውጤታማነትና ተጨባጭ ለውጥ ማስገኘቱንም ነው ያብራሩት። እነዚህ ስኬቶች ከሀገሪቱ የዐሥር ዓመት መሪ የልማት ዕቅድ፣ ከአፍሪካ ኅብረት የ2063 አጀንዳ እና ከዓለም አቀፉ የዘላቂ ልማት ግቦች ጋር የተናበቡ ሲሆን፣ የተቀረጹትም በጋራ ተሳትፎና ውህደት ላይ ተመስርቶ እንደሆነ አስረድተዋል። ወደፊትም ሀገራዊ ልማታችን በመረጃ ላይ የተመሠረተና ሁሉን አቀፍ እንዲሆን ለማድረግ ሰፊ የሪፎርም ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አንስተዋል። ከእነዚህም መካከል ፈጣንና ቀጥታ የመረጃ ሥርዓቶችን ማስፋፋት፣ የአስተዳደራዊ መዛግብትን ማቀናጀት፣ እንዲሁም በሰው ሠራሽ አስተውሎት፣ በሩቅ መረጃ ቅበላ እና በጂኦግራፊያዊ መረጃ ሥርዓት የሰው ኃይል አቅምን መገንባት ቀዳሚዎቹ ናቸው ብለዋል። ይህ በመረጃ ዘርፍ የተመዘገበው ሀገራዊ ሽግግር ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ዕውቅና እንድታገኝ ያስቻላት ሲሆን፣ ተቋማዊ ተሞክሮዋን ለሌሎች ሀገራት ማካፈል የምትችል አርዓያ እንዳደረጋትም ገልጸዋል።
በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የሚመራ ሉዓላዊ የዲጂታል ኢንተለጀንስ መሠረተ-ልማት እየተገነባ ነው
May 18, 2026 74
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የሚመራ ሉዓላዊ የዲጂታል ኢንተለጀንስ መሠረተ-ልማት እየተገነባ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሜሮን ከፈለው (ዶ/ር) ገለጹ። ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው ሀገራዊ ጉባኤ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት እየተካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሜሮን ከፈለው (ዶ/ር) የሀገሪቱ ብሔራዊ የስታቲስቲክስ ሥርዓት ስላደረገው የዲጂታል አሰራር ማብራሪያ ሰጥተዋል። ተቋሙ ከተበታተነ እና በእጅና በወረቀት ከሚሠራ አሠራር ወጥቶ፤ በኮምፒውተር የታገዘ የግል ቃለ-መጠይቅ ሥርዓት፣ የጂኦግራፊያዊ መረጃ ሥርዓት ውህደት፣ የሪሞት ሰንሲንግ፣ የክላውድ መሠረተ-ልማት፣ እንዲሁም ከኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር (ኢንሳ) ጋር በመተባበር በሀገር ውስጥ የቆጣሪዎች መከታተያ መድረክን በመጠቀም ወደ ሙሉ ዲጂታል እና ቅጽበታዊ (Real-time) የስታቲስቲክስ ሥነ-ምህዳር መሸጋገሩን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ አሁን ላይ መረጃ በመሰብሰብ ላይ ብቻ እንዳልተወሰነች፤ ይልቁንም 26 በሀገር አቀፍ ደረጃ የተገናኙ ቅርንጫፎችን፣ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) የሚመራ የጥናትና ቆጠራ የመረጃ ቋት፣ እንዲሁም በዘመናዊ መሠረተ-ልማት እምነት በሚጣልባቸው ስልቶች እና ብቃት ባለው የኢትዮጵያውያን የሰው ኃይል ላይ የተመሠረተ ግልጽ የፍኖተ ካርታ የያዘ ሉዓላዊ የዲጂታል ኢንተለጀንስ መሠረተ-ልማት እየገነባች መሆኑን በአጽንኦት ገልጸዋል።
''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ ሀገራዊ ጉባኤ እየተካሄደ ነው
May 18, 2026 108
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው ሀገራዊ ጉባኤ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት እየተካሄደ ይገኛል። ኢትዮጵያ የልማት ትልሞቿን እንዲሁም ስኬቶቿን በመረጃ እና በአሃዛዊ ማስረጃ መሰነድ ከጀመረች መሰነባበቷን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። ይህ እርምጃ ኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም በሌሎች በሚደገፉና በተበታተኑ የመረጃ ቋቶች ላይ የነበራትን ሙሉ ጥገኝነት ለመቅረፍ ያሳየችውን ከፍተኛ ቁርጠኝነት ማረጋገጫ መሆኑን አመልክቷል። ይህ አዲስ ምዕራፍ የሀገሪቱን የመረጃ ሉዓላዊነት በተግባር በማረጋገጥ፣ ኢትዮጵያ በራሷ መረጃ ላይ ተመስርታ እንድትወስንና የራሷን የልማት መስመር እንድትተልም አስችሏታል። በዚህም መሠረት፤ በዛሬው ጉባኤ ላይ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ልማትና የመረጃ ሉዓላዊነት ጉዞ ያመጣቸው ስኬቶችና የወደፊት አቅጣጫዎች በጥልቀት እንደሚዳሰሱ ጽህፈት ቤቱ ገልጿል።
የከተሞችን መሬት በአግባቡ ለማስተዳደርና ዘመናዊ አገልገሎት መስጠት የሚያስችል የመሬት ዲጂታል አድራሻ ተግባራዊ እየተደረገ ነው
May 16, 2026 494
አዳማ፤ ግንቦት 8/2018(ኢዜአ)፦ የከተሞችን የመሬት ሃብት በአግባቡ ለማስተዳደርና ዘመናዊ አገልገሎት መስጠት የሚያስችል የመሬት ዲጂታል አድራሻ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አብዱልአዚዝ ዳውድ (ዶ/ር) ገለጹ። በአዳማ ከተማ የመሬት ሃብትን በአግባቡ ማስተዳደርና የአገልግሎት አሰጣጥን ማዘመን የሚያስችል የመሬት ዲጂታል አድራሻ ትግበራ ፕሮጀክት በዛሬው እለት ተመርቆ በይፋ አገልግሎት መስጠት የጀመረ ሲሆን የዲጂታል ማፕ ርክክብም ተደርጓል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አብዱልአዚዝ ዳውድ (ዶ/ር)፤ በከተሞች የመሬት ሀብትን በአግባቡ ማስተዳደር የሚያስችል በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፈ አሰራር ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። በከተሞች ዜጎች ለንብረታቸው ዋስትና እንዲያገኙ፣ የኢንቨስትመንት ፍሰትን ለመጨመርና ስማርት መሰረተ ልማት ለማስፋፋት የመሬት ትራንስፎርሜሽንና ዲጂታል አድራሻ ትግበራ አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም በአዳማ ከተማ የመሬት ሃብትን በአግባቡ ማስተዳደር የሚያስችል የመሬት ዲጂታል አድራሻ ተግባራዊ ተደርጓል ብለዋል። በአዳማ ከተማ ዘመናዊ የመሬት አስተዳደር ስርዓት በመተግበርና የካዳስተር ስርዓት ወደ ስራ በማስገባት ቀዳሚና ብዙ ልምድ የተገኘበት እንደሆነም ገልጸዋል። በቀጣይም በከተሞች ቴክኖሎጂን የማስፋፋትና ወደ ስራ በማስገባት የአገልግሎት አሰጣጥን ዘመናዊ፣ ፈጣንና ቀልጣፋ የማድረግ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ምክትል ዳይሬክተር ዳንኤል ጉታ፤ የአዳማ የዲጂታል መሬት ትራንስፎርሜሽን ስርዓት የከተማዋ ለዲጂታል ዕድገት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በመተባበርም የመሬት ካዳስተር ስርዓት እውን እንዲሆን ማገዙን አንስተው በዛሬው እለት ተመርቆ ወደ ተግባር የገባው ፕሮጀክትም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው መሆኑን ተናግረዋል። እንዲህ አይነት ትግበራዎች የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 እቅድን ለማሳካት መሰረት የሚጥሉ መሆናቸውን አስረድተዋል። የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ (ዶ/ር)፤ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ፕሮግራም በ73 ከተሞች የመሬት ዲጂታል አድራሻ ለመገንባት እየተሰራ ነው ብለዋል። የአዳማን ጨምሮ የዘጠኝ ከተሞች የዲጂታል አድራሻ ግንባታ መጠናቀቁን ገልጸው የ32 ከተሞች የዲጂታል አድራሻ ግንባታ ስራ እየተከናወነ ይገኛል ነው ያሉት። የአዳማ ከተማ ዲጂታል አድራሻ የመሬት፣ የትራንስፖርት፣ የገቢ፣ የንግድና ሌሎች አገልግሎቶችን ዜጎች በተንቀሳቃሽ ስልክ ካሉበት ሆነው እንዲገለገሉ ያስችላል ብለዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ፤ ባለፉት አምስት ዓመታት የስማርት አዳማ ፕሮግራም በመቅረጽና በመተግበር ስኬታማ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። የአገልግሎት አሰጣጥን በማዘመንና ዲጂታል በማድረግ የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ስርዓትን ከማዘመን ባለፈ የሃብት ምዝበራ እንዳይከናወን ማድረግ ተችሏል ብለዋል። በዚህም የኢንቨስትመንት ፍሰቱ እንዲጨምር፣ በመሬት አካባቢ የነበረውን ህገ ወጥ አሰራር የመከላከልና የገቢ አቅምን ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል።
ከኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የሚገኝ የቴክኖሎጂ እውቀት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ያስችላል
May 16, 2026 318
ደብረ ብርሃን፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ) ፡-የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የወጣቱን የቴክኖሎጂ እውቀትና ክሕሎት እያሳደገ መሆኑን የሰሜን ሸዋ ዞን አስተዳደር ጽህፈት ቤት ገለፀ። በሰሜን ሸዋ ዞን አስተዳደር ጽሕፈት ቤት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቡድን መሪ አቶ ደመላሽ በላይ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና የወጣቱን የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎት በማሳደግ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን እየጨመረ ይገኛል። በዋናነትም የወጣቱን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ እና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ሰፊ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አመልክተዋል። ሥልጠናው በተለይ ወጣቱን በአንድሮይድ ማበልጸግ፣ በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በዳታ ሳይንስና በሰው ሠራሽ አስተውሎት (ኤ አይ) መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት ባለቤት እንዲሆን ማድረጉንም አብራርተዋል። በዞኑ በተያዘው በጀት ዓመት 30 ሺህ ለሚደርሱ ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና ለመስጠት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም ከ20 ሺህ በላይ ሰዎች ሥልጠናውን መውሰዳቸውን የገለጹት አቶ ደመላሽ፤ ሌሎች 10 ሺህ የሚደርሱት ደግሞ ሥልጠናውን በመከታተል ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ሥልጠናውን ካጠናቀቁት መካከል 90 የሚሆኑት በቀሰሙት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ዕውቀት የራሳቸውን ሥራ መፍጠራቸውንም ተናግረዋል። የደብረ ብርሃን ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ ምክትል ዲን አቶ አየለ ፍሥሐ በበኩላቸው እንዳሉት፤ የኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና ወጣቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ብቃት ያለው የዲጂታል ክህሎት እንዲኖረው እያደረገ ነው። ሥልጠናው በሀገሪቱ እያደገ የመጣውን የኢንዱስትሪ ዘርፍ በብቁና ተወዳዳሪ የሰው ኃይል ከመደገፍ ባሻገር፣ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የሚያስችል እንደሆነ ገልጸዋል። በዘርፉ የበቃ የሰው ኃይል ለማፍራት በሚደረገው ጥረትም በትብብር እየተሠራ መሆኑን አንስተው፣ ይህም የበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ሥልጠናውን ከወሰዱት ወጣቶች መካከል የደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪው ወጣት ዳዊት ዳምጠው፤ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ የዩኒቨርሲቲ ምሩቅ ሲሆን፣ የኮደርስ ሥልጠና በመውሰድ ተጨማሪ ዕውቀትና ክህሎት ማዳበሩን ይናገራል። በዚህም «አቢሲኒያ ዲጂታል» የተሰኘ ሲስተም በማበልጸግ ተጨማሪ ገቢ እያገኘ መሆኑን ገልጿል። ሥልጠናው ዘመኑ የሚሻውን ቴክኖሎጂ ተጠቅሞ ሀገርን፣ አካባቢንና ራስን ተጠቃሚ ለማድረግ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው በመሆኑ፣ ሌሎች ወጣቶችም ዕድሉን ሊጠቀሙበት ይገባል ሲል መክሯል። ወጣት መክሊት ጌቱ በበኩሏ፤ ሥልጠናው የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎቷን ለማሳደግ እንዳገዛት አንስታ፣ በቀጣይም በዘርፉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ለመሰማራት ማቀዷን ተናግራለች።
የዩኒቨርሲቲው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ትግበራ የልዩ ፍላጎት ትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ለማሳካት እያገዘ ነው
May 16, 2026 295
ዲላ፤ ግንቦት 8/2018(ኢዜአ)፦ የዲላ ዩኒቨርሲቲ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ትግበራ የልዩ ፍላጎት ትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ለማሳካት እያገዘ መሆኑ ተገልጿል። የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ታምራት በየነ (ዶ/ር) እንዳሉት የዩኒቨርሲቲው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ትግበራ የመማር ማስተማር ሂደቱን ከማቀላጠፍ ባለፈ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት እያገዘ ነው። ዩኒቨርሲቲው ዲጂታል ቴክኖሎጂን በመተግበር ልዩ ፍላጎት ያላቸው ተማሪዎችን የትምህርት አቀባበል ለማሳደግ በትኩረት ሲሰራ መቆየቱንም ተናግረዋል። ይህም የልዩ ፍላጎት ትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ለማሳደግ አቅም መፍጠሩን አመልክተዋል። በዩኒቨርሲቲው የልዩ ፍላጎትና አካቶ ትምህርት ክፍል ዳይሬክተር መምህርና ተመራማሪ አባቡ ተሾመ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት የዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራ ልዩ ፍላጎት ያላቸው የማህበረሰብ ክፍሎችን የልማት ተሳትፎ እያሳደገ ነው። በተለይም ተማሪዎቹ በዲጂታል ቴክኖሎጂ የሚታገዙበትን አካታች ስርአት ለመዘርጋት ማስቻሉን ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው ተግባራዊ ያደረገው ጽሁፍን ወደ ብሬል የሚቀይር ቴክኖሎጂ፣ የልዩ ፍላጎት ተማሪዎችን የዲጂታል አቅም የማሳደግ ተግባር እንዲሁም የዲጂታል ቤተ መጽሐፍት አገልግሎቶችን ተደራሽነት በማሳያነት ጠቅሰዋል። የዩኒቨርሲቲው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ተደራሽነት የልዩ ፍላጎትና አካቶ ትምህርትን ለማቀላጠፍ የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከቱን ያነሱት ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የሥነ ትምህርት መምህርና ተመራማሪ ወንድወሰን ገበያው (ዶ/ር) ናቸው። ለዚህም የተማሪዎችን የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎት ማሳደግና መሰረተ ልማትን ማሟላት ላይ ወሳኝ ሥራ መከናወኑን ጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው የዘረጋው የዲጂታል ተክኖሎጂ ትግበራ ልዩ ፍላጎት ያላቸው ተማሪዎችን ተወዳዳሪነት የሚያሳድግ ነው ያለው ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የልዩ ፍላጎት ትምህርት ክፍል 3ኛ ዓመት ተማሪ ኢስማኤል ሽፍ ነው። ዩኒቨርሲቲው የዲጂታል ተክኖሎጂ ተደራሽነትን ከማስፋት ባለፈ ልዩ ፍላጎት ያላቸውን ተማሪዎች የሚያስተናግድ የመማር ማስተማር ምህዳር መፍጠሩ ለሌሎች አርአያ እንደሚሆንም ገልጿል። ቴክኖሎጂው ትምህርታቸውን በቀላሉ እንዲከታተሉ በማድረግ ውጤታማ እንዳደረጋቸውም ጨምሮ ተናግሯል።
ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ስራው በተጓዳኝ ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ የሚያግዙ የምርምር ስራዎች እያከናወነ ነው
May 15, 2026 426
አዳማ፣ ግንቦት 7/2018(ኢዜአ)፦ የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ስራው በተጓዳኝ ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ የሚያግዙ የምርምር ስራዎች እያከናወነ መሆኑን ገለጸ። ችግር ፈቺ ምርምሮች የሚቀርቡበት 4ኛው ሀገር አቀፍ የጥናትና ምርምር ኮንፈረንስ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በመካሄድ ላይ ይገኛል። የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ለሚ ጉታ፤ ዩኒቨርሲቲው ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት እያከናወነ ካለው የመማር ማስተማር ስራ በተጓዳኝ ዘርፈ ብዙ የማህበረሰብ ችግር ፈቺ ምርምሮችን በማከናወን ላይ ይገኛል ብለዋል። በተለይ ከአካባቢና ተፈጥሮ ጋር የሚስማማ የተቀናጀ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ልማትና አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ ሀገሪቱ እያደረገች ያለችውን ጥረት በሙያ፣ በዕውቀትና በምርምር እየደገፈ እንደሚገኝ ገልጸዋል። አሰራርና አገልግሎትን ለማዘመን፣ በመሰረተ ልማት ዝርጋታና በልማት ፕሮጀክቶች ጭምር በማማከር እያገዘ እንደሚገኝም ተናግረዋል። በአካባቢ ጥበቃና በተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም፣ በአፈር ለምነት፣ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማትና ግንባታ ዙሪያ የተለያዩ የምርምር ስራዎችን በማከናወን የመፍትሔ ሐሳቦች እየጠቆመ መሆኑንም ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው አዳማ ከተማን ጨምሮ በቢሾፍቱና በሸገር ከተማ እየተገነቡ ያሉ የዲጂታል ቴክኖሎጂና አገልግሎቶች የማዘመን ስራን በሙያ፣ በዕውቀትና በምርምር እያገዘ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው የዘላቂ ልማት ግቦችን ለማሳካት የምርምር ፓርክ በመገንባት፣ በአሁኑ ወቅት በዘመናዊ የምርምር ቴክኖሎጂ፣ በላቦራቶሪዎችና በመሳሪያዎች እያደራጀ መሆኑንም ጠቁመዋል። በኮንፈረንሱ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ዶክተር መስፍን ነገዎ እንደገለጹት፤ ሀገሪቱ የጀመረችውን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እውን ለማድረግ የሚደረገውን ጥረት ዩኒቨርሲቲዎች በምርምር መደገፍ አለባቸው። ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በምርምር የተደገፉ አመላካች መፍትሄዎችን በማቅረብ ለአሰራር፣ ለስትራቴጂና ለፖሊሲ ግብዓት እንዲሆኑ ማገዝ እንደሚገባቸውም ተናግረዋል። በተለይ መንግሥት አገልግሎቶችን ለማዘመን የጀመረው የዲጂታል ቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ዝርጋታ እንዲሳካ ዩኒቨርሲቲው እያደረገ ያለው ጥረት አበረታች መሆኑን ጠቅሰዋል። በኢንዱስትሪ ትስስር፣ በኢንጂነሪንግና ቴክኖሎጂ ልማት፣ በማህበረሰብ አገልግሎቶች እንዲሁም በምርምር ፓርክና በልህቀት ማዕከላት በማደራጀት ወደ ቀጣይ ምዕራፍ ለመሻገር እያደረገ ያለው ጉዞ የሚደነቅ መሆኑንም አክለው ገልጸዋል። በተለይ የዲጂታል አገልግሎትን ጨምሮ የስማርት መሰረተ ልማት ዝርጋታን በሳይንሳዊ ምርምር በመደገፍ እያደረገ ያለውን ጥረት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም አሳስበዋል። በዩኒቨርሲቲው የአካባቢ ጥበቃና የተፈጥሮ ሀብት መምህር ዶክተር ኬይረዲን ተማም እንደተናገሩት፤ በሀገሪቱ የተጀመሩ የስማርት መሰረተ ልማት ፕሮግራሞችን በምርምር ለመደገፍ ጥረት እየተደረገ ይገኛል። አካታችና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ የአየር ንብረት ተፅዕኖን መቋቋም የሚችል ስማርት መሰረተ ልማት ማስፋፋት ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ ዘመናዊ መሰረተ ልማት መገንባት ለዘላቂ ልማት መረጋገጥ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ቀናት በሚቆየው ኮንፈረንስ ላይ ከተለያዩ የምርምር ተቋማት፣ ከሀገር ውስጥና ከውጭ ሀገራት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የተወጣጡ ተመራማሪዎችና ምሁራን ተሳታፊ ሆነዋል።
አሶሳ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ በርካታ የምርምር ስራዎችን እያከናወነ ነው
May 15, 2026 223
አሶሳ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ አሶሳ ዩኒቨርሲቲ በምርምር እና ቴክኖሎጂ ሽግግር መስክ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራት የማህበረሰቡን ችግሮች በመፍታት ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያሳዩ መሆናቸውን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ከማል አብዱራሂም አስታወቁ። ዩኒቨርሲቲው 11ኛውን ዓመታዊ የምርምር ኮንፍረንስ እያካሄደ ነው። በኮንፍረንሱ መክፈቻ ላይ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ከማል አብዱራሂም (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ተቋሙ በተሰጠው የአፕላይድ ሳይንስ የትምህርት መስክ ትኩረት አድርጎ እየሰራ ይገኛል። በዚህም በግብርና፣ በማዕድን እና በቴክኖሎጂ ሽግግር ዘርፎች ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ የምርምር ስራዎች መከናወናቸውን አብራርተዋል። ዩኒቨርሲቲው በተለይም በግብርናው ዘርፍ ያከናወናቸው የምርምር ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን የጠቀሱት ፕሬዝዳንቱ፤ በተሻሻሉ የሰብልና የእንስሳት ዝርያዎች፣ በማንጎ በሽታ መከላከል እንዲሁም በቀርከሃ ሀብት ልማት ዙሪያ የተሰሩ ስራዎች የአርሶ አደሩን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት እያሳደጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። እነዚህ የምርምር ውጤቶች በቀጥታ ወደ አርሶ አደሩ ማሳ እንዲወርዱ በመደረጉም በአካባቢው ምርትና ምርታማነት ላይ አዎንታዊ ተጽዕኖ መፍጠራቸውን አብራርተዋል። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሁሉም ዘርፍ የሚያከናውኗቸው የምርምር ስራዎች የማህበረሰቡን ችግሮች ከመፍታት ባለፈ፣ ለሀገራዊ የፖሊሲ ቀረጻ በግብዓትነት ማገልገል እንደሚገባቸውም ዶክተር ከማል ተናግረዋል። የዩኒቨርሲቲው የምርምር እና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት ዑመር ሸሪፍ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው እያከናወናቸው የሚገኙ የምርምር ስራዎች የህብረተሰቡን ችግር ከመፍታት ባለፈ ለተመራማሪዎች አቅም ግንባታ ትልቅ ፋይዳ እንዳላቸው ገልጸዋል። እንደ ምክትል ፕሬዚዳንቱ ገለጻ፣ የምርምር ስራዎቹ ተመራማሪዎች በተግባር የተደገፈ እውቀት እንዲያዳብሩና በዓለም አቀፍ የሳይንስ መድረኮች ላይ ተወዳዳሪ መሆን እንዲችሉ ሰፊ ዕድል ፈጥሮላቸዋል። ለሁለት ቀናት በሚቆየው በዚህ የምርምር ኮንፈረንስ ላይ በግብርና፣ በማዕድን፣ በቴክኖሎጂ እና በሌሎች ቁልፍ ዘርፎች ላይ የተከናወኑ የምርምር ስራዎች ለውይይት እንደሚቀርቡ ይጠበቃል። በምርምር ውጤቶቹ ላይ የሚደረገው ጥልቅ ውይይትም በቀጣይ ለሚከናወኑ የልማት ስራዎች እና ለቴክኖሎጂ ሽግግር ሂደቱ ይበልጥ መጠናከር እንደ አቅጣጫ የሚያገለግሉ ግብዓቶች እንደሚገኙበት ታምኖበታል።
የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን ሥራ ላይ በማዋል ተጨባጭ ውጤቶች እየተገኙ ነው
May 15, 2026 228
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ዓለም አቀፍ ስታንዳርድ የጠበቀ የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን ሥራ ላይ በማዋል ተጨባጭ ውጤቶች እየተገኙ መሆኑን የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር እና የዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት የአፍሪካ አህጉር ፕሬዚዳንት አቶ ፈጠነ ተሾመ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኢንስቲትዩቱ የትንበያ አቅም በሰው ኃይል፣ በቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ዝርጋታና በተደራሽነት ረገድ ወደ ላቀ ደረጃ እየተሸጋገረ ይገኛል። በአሁኑ ወቅትም የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ የአየር ሁኔታ ትንበያዎችን ለውሳኔ ሰጪ አካላትና ለተጠቃሚው ማኅበረሰብ በወቅቱ ተደራሽ እያደረገ መሆኑንም ገልጸዋል። ኢንስቲትዩቱ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ለመስጠት ካስቀመጠው ግብ አንጻር፣ ግቡን ለማሳካት የሚያስችሉ ሁለንተናዊ የሚቲዎሮሎጂ ምልከታ መሠረተ ልማቶች በአገር አቀፍ ደረጃ መዘርጋታቸውን ጠቁመዋል። የአየር ሁኔታን በቅርበት ለመከታተል የሚያስችሉ ዘመናዊ ራዳሮች በአራት ስትራቴጂካዊ የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ ተተክለው በቅርቡ ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመዋል፡፡ ራዳሮቹ የተተከሉባቸው ቀጠናዎች በሰሜን ምዕራብ ኢትዮጵያ፣ በምዕራብ ኢትዮጵያ፣ በመካከለኛው ኢትዮጵያ እና በደቡብ ኢትዮጵያ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ እነዚህ ዘመናዊ ራዳሮች በተተከሉበት ስፍራ ዙሪያ እስከ 250 ኪሎ ሜትር ክብ ርቀት (ራዲየስ) ውስጥ ያለውን ማንኛውንም የሚቲዎሮሎጂ ለውጥና መረጃ በቀጥታ ወደ ማዕከላዊ የመረጃ ቋት የመላክ ከፍተኛ አቅም እንዳላቸው አብራርተዋል። ከራዳር ዝርጋታው በተጨማሪ፣ የአየር ንብረት መረጃዎችን በከፍተኛ ፍጥነት ወደ መረጃ ቋት የመላክ አቅም ያላቸው የ‘አውቶማቲክ ዌዘር ስቴሽኖች’ ተከላ እየተካሄደ መሆኑን አንስተዋል። እነዚህ ወደ ሥራ የገቡና እየተዘረጉ ያሉ ቴክኖሎጂዎች ዓለም የደረሰበትን ከፍተኛ የሚቲዎሮሎጂ ምልከታ ደረጃ የጠበቁ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም የአገሪቱን የትንበያና የቅድመ ማስጠንቀቂያ አቅም በማጎልበት ረገድ የሚጫወቱት ሚና ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል። ቴክኖሎጂዎቹ ተደራሽነትን ከማስፋታቸውም በላይ ማኅበረሰቡ ወቅቱን የጠበቀና አስተማማኝ አገልግሎት እንዲያገኝ እንደሚያስችሉ አስገንዝበዋል። የቴክኖሎጂ ውጤቶቹ ለግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ፣ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ ሊከሰት የሚችለውን ጉዳት በቅድመ ማስጠንቀቂያ ለመቀነስ ብሎም ለሌሎች መሠረታዊ ጉዳየች ያላቸው ፋይዳ የጎላ ነው፡፡
የምርምር ማዕከሉ የመድኃኒት ምርምርና ስርጸት ውጤታማነትን የሚያሳድግ አዲስ አቅም እየፈጠረ ነው
May 14, 2026 341
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፦በአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት የተገነባው የምርምር ማዕከል የመድኃኒት ምርምርና ስርጸት ውጤታማነትን የሚያሳድግ አዲስ አቅም መፍጠሩን የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር መሳይ ወልደማርያም ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት በዘመናዊ መልክ የተገነባውን የምርምር ማዕከል መጋቢት 26 ቀን 2018 ዓ.ም መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። በአርማወር ሐንሰን የምርምር ተቋም ቅጥር ግቢ የተገነባው ዘመናዊ ተቋም ከመሠረተ ልማት ግንባታ ባለፈ፤ ራሷን የቻለችና ጤናማ የሆነች ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ የሚተጋ የላቀ የዕውቀት ማዕከል ነው። የምርምር ማዕከሉም 40 ላቦራቶሪዎችን፣ የላቁ የጂኖሚክስ እና የባዮ ኢንፎርማቲክስ፣ በሀገር ውስጥ የሚመረቱ መድኃኒቶችን ጥራትና ብቃት የሚያረጋግጥ የባዮ ኢኩዊቫለንስ ማዕከላትን አካቷል። የተለያዩ የመድኃኒት አምራች ኩባንያዎችም በአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት በዘመናዊ መልክ የተገነባውን የምርምር ማዕከል ጎብኝተዋል። የአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር መሳይ ወልደማርያም፤ ጉብኝቱ የሚበለፅጉ የምርምር ውጤቶች ሽግግር ውጤታማነትን ለማስጠበቅ ያለመ ነው ብለዋል። ማዕከሉ የመድኃኒት ምርምርና ስርጸት ተወዳዳሪነትን በማሳደግ ከፍተኛ አቅም እንደሚሆን ገልጸዋል። በማዕከሉም የመድኃኒት ምርምርና ስርጸት ሥራዎችን በላቀ መንገድ ማከናወን የሚያስችል አዲስ አቅም መፍጠር እንደተቻለ ተናግረዋል። በምስራቅ አፍሪካ ብቸኛው የመድኃኒት ተነጻጻሪነት ፍተሻ በማዕከሉ መገንባቱም ከኢትዮጵያ ባሻገር ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር የላብራቶሪ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል አንስተዋል። የአርማወር ሐንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት የሀገር በቀል ዕውቀቶችን መነሻ በማድረግ የተለያዩ በሽታዎችን ሕክምና መስጠት የሚያስችሉ ስምንት የምርምር ውጤቶች መበልፀጋቸውን ገልጸዋል። በምርምር የበለፀጉ ውጤቶችም እንደ ዋና ንጥረ ነገር የሚያገለግሉና ክትባትን በተሻሻለ ቴክኖሎጂ መስጠት የሚያስችሉ መሆናቸውን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ መድኃኒት አምራቾች ማኅበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ታደሰ ተፈሪ፤ በኢትዮጵያ በፖሊሲ ማዕቀፍና በተለያዩ የማሻሻያ እርምጃዎች የተሻለ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል። የምርምር ማዕከሉም የኢትዮጵያን የጤና ዘርፍ የጥናትና ምርምር ውጤታማነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑን ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ከተማ የባህል ሕክምና አዋቂዎች ማኅበር ፕሬዝዳንት መጋቤ ጥበብ መሪጌታ መንግስቱ ደስታ በበኩላቸው፤ ማዕከሉ የባህል ሕክምና ውጤታማነትን ለማሳደግ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። ማዕከሉ በዘርፉ የተሰማሩ ኢንዱስትሪዎችን የሚያግዝ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የኢትዮጵያ አነስተኛ መድኃኒት አምራቾች ዘርፍ ማኅበር ፕሬዝዳንት ሀሺም አሕመድ ናቸው። የዜኒት ገብስ እሸት ኢትዮጵያ ምክትል ዋና ሥራ አስኪያጅ ሰለሞን ገብረእግዚእ በበኩላቸው፤ በማዕከሉ የተፈጠረው የምርምር ምኅዳር የመድኃኒት አምራቾችን አቅም ለማጎልበት እንደሚያግዝ ገልጸዋል።
አሶሳ ዩኒቨርሲቲ የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎችን ለአርሶ አደሮች እያሰራጨ ነው
May 14, 2026 316
አሶሳ፤ ግንቦት 5/2018(ኢዜአ)፦ ከአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ያገኟቸው የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎች በእንስሳት እርባታ ስራቸው የበለጠ ውጤታማ እንደሚያደርጋቸው በአሶሳ ዞን የኡራ ወረዳ አርሶአደሮች ተናገሩ። የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የምርምር ማዕከል የተሻሻሉ የፍየል ዝርያዎችን በኡራ ወረዳ ለሚገኙ አርሶአደሮች አሰራጭቷል። ዩኒቨርሲቲው በረጅም ጊዜ ምርምር ያገኛቸውና ለአርሶ አደሮቹ ያሰራጫቸው ፍየሎች በዓመት ከሁለት ጊዜ በላይ መንታ ግልገሎችን የሚወልዱና በሽታን የሚቋቋሙ መሆናቸውም ተገልጿል። ፍየሎቹን የተረከቡት የወረዳው አርሶአደሮች ለኢዜአ እንደሚሉት፤ የእንስሳት ዝርያዎቹ በምርታማነታቸውም ሆነ በሽታን በመቋቋም ረገድ ካሏቸው ጠቀሜታ አንጻር የኑሮ ደረጃቸውን ለማሻሻል ከፍተኛ ሚና ይጫወታሉ። የተሻሻሉ የፍየል ዝርያ ማግኘታቸው የእንስሳት እርባታ ዘርፍን በሳይንሳዊ መንገድ በማከናወን የበለጠ ውጤታማ እንደሚያደርጋቸውም ተናግረዋል። አርሶአደር ዘካሪያ መርሱቅ እና ዘይነብ መኮነን በአሁኑ ወቅት የሚያረቧቸውን ፍየሎች አስፈላጊውን እንክብካቤ እያደረጉላቸው እንደሆነ ገልፀው ከዩኒቨርሲቲው ያገኟቸው ፍየሎች ደግሞ የእንስሳት እርባታ ስራቸውን በተሻለ መልኩ ለመስራት ዕድል እንደሚፈጥርላቸው ተናግረዋል። ለፍየል ዝርያዎቹ አስፈላጊውን ጥበቃ በማድረግና አብዝተው በማርባት ከራሳቸው ባለፈ ለሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ተደራሽ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውንም ገልጸዋል። ሌላው አርሶአደር ሙሐመድ ሳሌ በበኩላቸው፤ ከዩኒቨርሲቲው ባገኙት የተሻሻለ የፍየል ዝርያ በእንስሳት እርባታ ዘርፍ በስፋት ለመሰማራት ማቀዳቸውን ተናግረዋል። የእንስሳት መኖ እና መጠለያ በማዘጋጀት ከወዲሁ በእርባታው ዘርፍ ውጤታማ ለመሆን እየሰሩ መሆናቸውንም አብራርተዋል። የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የተሻሻሉ የሰብል እና የእንስሳት ዝርያዎችን ለአርሶአደሩ በማድረስ ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ ነው ያሉት ደግሞ የኡራ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ታጀዲን ሙሐመድ ናቸው። ዩኒቨርሲቲው ከዚህ በፊት በምርምር ያወጣቸው የጤፍ ዝርያ የወረዳውን አርሶአደሮች ተጠቃሚ ያደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ አሁንም የእንስሳት እርባታ ዘርፍን በማዘመን ምርታማነትን ለማሳደግ የጀመረው የምርምር ስራ የሚደነቅ ነው ብለዋል። የተሻሻሉ የፍየል ዝርያዎችን የተረከቡ አርሶአደሮች ውጤታማ እንዲሆኑ የወረዳው አስተዳደር አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል።
የግለሰቦችን የግል መረጃ ለታለመለት ዓላማ ብቻ ማዋል የሚያስችል የተጠናከረ የግል ዳታ ጥበቃ እየተከናወነ ነው
May 13, 2026 351
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2018 (ኢዜአ)፦ተቋማት የግለሰቦችን የግል መረጃ ለታለመለት ዓላማ ብቻ ጥቅም ላይ እንዲያውሉ የሚያስችል የተጠናከረ የግል ዳታ ጥበቃ እየተከናወነ መሆኑን የኢትዮጵያ ኮሙኒኬሽን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ባልቻ ሬባ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ኮሙኒኬሽን ባለስልጣን የግል ዳታ ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 1321/2016 ትግበራና አፈጻጸምን በተመለከተ ከባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ አካሂዷል። የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ባልቻ ሬባ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ተቋሙ በህግ በተሰጠው ሥልጣን መሰረት ለግለሰቦች መረጃ የግል ዳታ ጥበቃ እየተደረገ ነው ብለዋል። በዓለም ላይ እየታየ የመጣው ፈጣን የቴክኖሎጂ ዕድገት ለአዋጁ መውጣት ምክንያት መሆኑን ገልጸው፤ የግል መረጃዎች በአግባቡ ካልተያዙ ላልተፈለገ ዓላማ በመዋል የግለሰቦችን መብት እንዲጣስ ያደርጋል ብለዋል፡፡ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካል የሆነው የግል ዳታ ጥበቃ ሀገራዊ ፖሊሲ ለመቅረጽና ስትራቴጅ ለመንደፍ ግብዓት ሆኖ እንደሚያገለግል ተናግረዋል። ተቋማትም የግለሰቦችን ዳታ ህጋዊ እና ሃላፊነት በተሞላበት አግባብ መጠቀም እና መጠበቅ እንዳለባቸው ገልጸዋል። የግለሰቦችን መረጃ ከታለመለት ዓላማ ውጭ የሚጠቀሙ ተቋማት ተጠያቂ የሚሆኑበት አሰራር እንዳለ ገልጸው፤ ግለሰቦች የግል ዳታ ጥሰት ሲያጋጥማቸው ለተቆጣጣሪው አካል ሪፖርት የሚያደርጉበት ፖርታል ተዘጋጅቷል ብለዋል። በኢትዮጵያ አየር መንገድ የሳይበር ደህንነት ከፍተኛ ተንታኝ ቤተልሔም መንግስቱ አየር መንገዱ በግል ዳታ ጥበቃ ዙሪያ የካበተ ልምድ እንዳለው ገልጸዋል። በተቋሙ በየጊዜው በግል ዳታ ጥበቃ ማዕቀፉ ዙሪያ ለሰራተኞቹ ግንዛቤ እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የህግና ፖሊሲ ዳይሬክተር ሳሙዔል ዓለሙ፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ 42 ሚሊዮን ዜጎች ብሔራዊ ድጂታል መታወቂያ መውሰዳቸውን ገልጸዋል። በምዝገባ ወቅት ከግለሰቦች የሚወሰዱ ዳታዎች ለታለመላቸው ዓላማ ብቻ እንዲውሉ ጥበቃ ይደረጋል ብለዋል፡፡ በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የዋና ዳይሬክተር ልዩ አማካሪ ፍቅረ ሥላሴ ጌታቸው በበኩላቸው፤ የግል ዳታ ጥበቃ ለዲጂታል ሽግግር መሰረት መሆኑን አንስተዋል። በግለሰቦችና ተቋማት መካከል መተማመን መፍጠር እንደሚያስችል አብራርተዋል፡፡
የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ሳይንስ ሙዚየምን ጎበኙ
May 13, 2026 357
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2018 (ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን በሳይንስ ሙዚየም ጉብኝት አድርገዋል። የሁለቱ ሀገራት መሪዎች በሳይንስ ሙዚየም ያደረጉት ጉብኝት፤ ለሁለቱ ሃገራት የመጪው ዘመን የላቀ ፈጠራ፣ ቴክኖሎጂ እና ከፊት ላሉ ሰፊ ዕድሎች ያላቸውን የጋራ ቁርጠኝነት ያንጸባረቁበት መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። ጉብኝቱ ተሻጋሪ ርዕይን የሰነቀ አጋርነት፤ ኢትዮጵያና ፈረንሳይ መጻኢ ጉዟቸው ብሩህ መሆኑን የሚያመለክት መሆኑም ተገልጿል።