ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 የባንኮችን አገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን ውጤታማ የፋይናንስ ሥርዓት እንዲኖር አድርጓል
Jan 29, 2026 271
ወልቂጤ፤ ጥር 21/2018 (ኢዜአ)፡- ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 የባንኮችን አገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን ውጤታማ የፋይናንስ ሥርዓት እንዲኖር ማገዙን የባንክ የሥራ ኃላፊዎች ተናገሩ። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ አገልግሎት አሰጣጣቸውን ለማዘመንና አስተማማኝ ፋይናንስ ሥርዓትን ለመዘርጋት በማስቻሉ ተሞክሮውን በማስፋት ወደ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 መግባታቸውንም ለኢዜአ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የበኩር ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ ፀበሉ ይብጌታ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ ዜጎች ደኅንነታቸው የተጠበቁ መተግበሪያዎችን በመጠቀም ባሉበት ቦታ ሆነው ገንዘባቸውን ከመቆጠብ ባለፈ ለማንቀሳቀስ እንዲችሉ አድርጓል ብለዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በላቀ ደረጃና ጥራት ለማስቀጠል ያለፉ ስኬቶችን መሠረት በማድረግ ተግባሩን ለማስቀጠል እንደሚሠሩም ተናግረዋል።   የዳሽን ባንክ ሆሳዕና አካባቢ ሥራ አስኪያጅ መሪሁን መኮንን በበኩላቸው፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ የፋይናንስ ተቋማትን ከዲጂታል ቴክኖሎጂ ጋር በማስተሳሰር ጤናማ የፋይናንስ አሠራር እንዲጠናከር ማድረጉን አስታውቀዋል። የደንበኞችን ፍላጎት መሰረት ያደረገና ከወረቀት ነፃ የሆነ አገልግሎት በመስጠት በርካታ አገልግሎቶች ተደራሽ እንዲሆኑ ማድረጉንም ተናግረዋል። ምቹና አስተማማኝ የሆኑ አዳዲስ መተግበሪያዎች እየቀረቡ መሆኑን ጠቅሰው፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ትግበራም የባንኩን አሠራር በተሟላ መንገድ በዲጂታል የታገዘ በማድረግ ተወዳዳሪነቱን ከፍ እንደሚያደርገው አመልክተዋል፡፡   በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ የተቋማቸው የአሠራር ሥርዓት እና ለዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ ለውጦች የተገኙበት መሆኑን ያነሱት ደግሞ በእናት ባንክ የሆሳዕና ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ ፍፁም ወልዴ ናቸው። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ይፋ መደረግም በተለያየ መንገድ የሚዘዋወርና ለብክነት የሚዳረግ ገንዘብን በመቆጣጠር ረገድ የጎላ ሚና እንደሚያበረክት አመላክተዋል።   በኢትዮጵያ ልማት ባንክ የሕግ ባለሙያ የሆኑት መሃሩ ሙጎ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ የባንኮችን አሠራርና መረጃ አያያዝ በማዘመን የማጭበርበር ወንጀሎችን ለመከላከል ያግዛል ብለዋል።
በመልዕክት መላላኪያ መተግበሪያዎች ከሚፈጸሙ የሳይበር ጥቃቶች ራስን እንዴት መጠበቅ ይቻላል?
Jan 29, 2026 76
የበርካታ ዜጎች የዕለት ተዕለት የስራ እንቅስቃሴና ግንኙነት ከዲጂታል ሥርዓት ጋር በጥብቅ መተሳሰሩን ተከትሎ፣ በማህበራዊ ሚዲያ መተግበሪያዎች ላይ የሚፈጸሙ የሳይበር ጥቃቶችና መጭበርበሮች በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመሩ ይገኛሉ። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የተቀናጀ የሳይበር መከላከል አገልግሎት ዲቪዠን ኃላፊ አቤል ተመስገን፤ የዲጂታል መተግበሪያዎች አጠቃቀም ላይ በቂ ንቃተ ህሊና አለመኖር በግለሰቦችና በተቋማት ላይ የከፋ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ገልጸዋል። እንደ ኃላፊው ገለጻ፣ የሰው ሰራሽ አስተውሎትና መሰል የቴክኖሎጂ ምጥቀቶች ጥቃቱን "ኢ-ተገማች" እና ድንበር ተሻጋሪ አድርገውታል። የተጠቃሚዎች የደህንነት ንቃተ ህሊና ማነስ ደግሞ የተጋላጭነት ምጣኔውን ይበልጥ አስፍቶታል። በዚህም ምክንያት በቴሌግራም፣ ዋትስአፕ እና መሰል መተግበሪያዎች የግል አካውንቶች የመጠለፍ፣ ሚስጥራዊ መረጃዎች የመመንተፍ እንዲሁም የማጭበርበር ሰለባ የመሆን አደጋዎች በስፋት እየተስተዋሉ ነው። ተጠቃሚዎች ከመሰል ስጋቶች ራሳቸውን ለመጠበቅ የደህንነት ማስጠበቂያ ስልቶችን በአግባቡ ማወቅና መተግበር እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ለዚህም የሚከተሉትን ነጥቦች እንደ አብነት ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም በቀላሉ የማይገመት የይለፍ ቃል መጠቀም፣ ባለሁለት ደረጃ ማረጋገጫ አማራጭ በመጠቀም የአካውንት ደህንነትን ማስጠበቅ፣ የግልና የቢዝነስ አካውንቶችን ለይቶ መጠቀም እንዲሁም የመተግበሪያዎችን የደህንነት ማሻሻያ በወቅቱ መጫንን ጠቅሰዋል፡፡ እንደ አፍሪካ ህብረት ጉባዔ ያሉ ትልልቅ ሁነቶችን እንደ ዕድል በመጠቀም የሚላኩ አሳሳች ሊንኮችና መልዕክቶች እንደሚበራከቱ ገልጸው፤ ማንኛውንም ሊንክ ከመክፈት በፊት በተጠራጣሪነት መመልከትና ትክክለኛነቱን ማረጋገጥ የሁልጊዜ ልምድ ሊሆን እንደሚገባ መክረዋል። የሳይበር ጥቃት ሰለባ መሆን የግል ጉዳት ብቻ ሳይሆን በሌሎች ሰዎች ላይም የሰንሰለት ጉዳት እንደሚያስከትልና "እኔን ማን ይጠልፈኛል?" የሚል መዘናጋት ዋጋ እንደሚያስከፍልም አቶ አቤል አስጠንቅቀዋል። አካውንቱ የተጠለፈበት ሰው በፍጥነት በሌሎች አማራጮች ለአካባቢው ሰዎች ማሳወቅ ያለበት ሲሆን፣ መልዕክት የሚደርሳቸው ሰዎችም የገንዘብ ጥያቄም ሆነ ሌላ መረጃ ሲጠየቁ መጠራጠር እንዳለባቸው ጠቁመዋል። አንዴ ከተጠለፉ በኋላ የማህበራዊ ሚዲያ አካውንቶችን ለማስመለስ የሚወስደው ጊዜ ውስብስብ በመሆኑ ቅድመ ጥንቃቄው ወሳኝ መሆኑ ተመላክቷል። ማንኛውም የሳይበር ጥቃት ሙከራ ሲያጋጥም በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ነፃ የጥሪ መስመር 933 ላይ በመደወል ወይም በኢሜል ሪፖርት ማድረግ እንደሚቻል ተገልጿል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ዜጎች በመልዕክት መላላኪያ አማራጮች በሚፈጸሙ የሳይበር ጥቃቶች ተጋላጭ እንዳይሆኑ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል-የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር
Jan 28, 2026 142
አዲስ አበባ፤ ጥር 20/2018 (ኢዜአ)፦ ዜጎች በዋትሳፕ፣ በቴሌግራም እና በሌሎች የመልዕክት መላላኪያ አማራጮች ለሚፈጸሙ የሳይበር ጥቃቶች እና የማጭበርበር ድርጊቶች ተጋላጭ እንዳይሆኑ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር አሳሰበ። ማህበረሰቡ የሳይበር ደህንነት የማስጠበቅ ኃላፊነቱን እንዲወጣም ጥሪ አቅርቧል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ)፤በኢትዮጵያ የዲጂታል ትስስር መስፋፋትን ተከትሎ በዋትሳፕ (WhatsApp)፣ በቴሌግራም (Telegram) እና በሌሎች የመልዕክት መላላኪያ ፕላትፎርሞች አማካኝነት በዜጎች ላይ የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶችና የማጭበርበር ድርጊቶች በአሳሳቢ ሁኔታ እየጨመሩ መምጣታቸዉን በተለያዩ መንገዶች ማረጋገጥ መቻሉን ለኢዜአ በላከው መግለጫ አስታውቋል። በአሁኑ ወቅት በሀገሪቷ የሚካሄዱ የተለያዩ ሲምፖዚየሞችን፣ ዓለም አቀፍ መድረኮችን እና የኦንላይን ስብሰባዎችን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም፣ የሳይበር ወንጀለኞች የእነዚህን ኩነቶች ስም ለሀሰተኛ ድርጊቶቻቸው መጠቀሚያ እያደረጉት እንደሚገኙ አመልክቷል። እነዚህ አካላት የማህበረሰቡን የግል መረጃ ለመስረቅ፣ የባንክ ሂሳቦችን ለመመዝበር እና የዲጂታል ደህንነትን ለማናጋት በተቀናጀ መልኩ እየሰሩ መሆኑን አስተዳደሩ በክትትልና በምርመራ ማረጋገጡን ገልጿል። የሳይበር ጥቃቶች የሚፈጸሙት ማህበረሰቡ ትኩረት የሚሰጣቸውን "ተፈላጊ" እና "ወቅታዊ" የሆኑ ጉዳዮችን መነሻ በማድረግ በተዘረጋ ስልታዊ የማታለያ ዘዴ መሆኑን ተጠቁሟል። አጭበርባሪዎቹ "ለሲምፖዚየሙ ተሳታፊዎች የተዘጋጀ ነጻ የኢንተርኔት ፓኬጅ"፣ "ልዩ የስራ ቅጥር" ወይም "ይህ የስብሰባ መሳተፊያ ሊንክ ነው፤ ከፍተው ይግቡ" የሚሉ አሳሳችና ማራኪ መልዕክቶችን በማሰራጨት ተጠቃሚዎች በመልዕክቱ ውስጥ የተካተተውን ሊንክ (Link) እንዲጫኑ እንደሚያደርጉ የገለጸው አስተዳደሩ፥ ይህ ድርጊት ተጠቃሚው ሳያውቀው ወደ አጥፊ ተልዕኮ ወዳላቸዉ ድረ-ገጾች እንዲያመራና ለጥቃት ተጋላጭ እንዲሆን የሚያደርግ የመጀመሪያው የወንጀለኞች እርምጃ እንደሆነ አመልክቷል። ጥቃት አድራሾቹ የአንዳንድ ግለሰቦች የግንዛቤ እጥረትና ትኩረት ማጣት የተነሳ የሚላኩላቸውን ሊንኮችና መልዕክቶች በጥንቃቄ የመመርመር ዕድላቸው አነስተኛ መሆኑን ተከትሎ ወንጀለኞቹ ይህን ሁኔታ እንደ ምቹ አጋጣሚ እየተጠቀሙበት ይገኛሉ ነው ያለው። ይህ አይነቱ ጥቃት ከግለሰቦች መረጃ ስርቆት ባለፈ፣ በእጃቸው የሚገኙ ሚስጥራዊ መረጃዎች በጠላፊዎች እጅ እንዲወድቁ በማድረግ በሀገር ደህንነትና ሉዓላዊነት ላይ ከፍተኛ አደጋ የሚጋርጥ መሆኑን አስተዳደሩ በጥብቅ አሳስቧል። በዚህም ተጠቃሚዎች የተላከላቸውን ሊንክ ሲጫኑ ወይም የተጠየቁትን መረጃ ሲሞሉ፣ የዋትሳፕ ወይም የቴሌግራም አካውንታቸው ወዲያውኑ በጠላፊዎች ቁጥጥር ስር እንዲዉል እንደሚያደርግም ነው በመግለጫው ላይ የሰፈረው። ወንጀለኞቹ አንዴ የአንድን ሰው አካውንት ከተቆጣጠሩ በኋላ፣ የተጠለፈውን አካውንት በመጠቀም በተጎጂው ስም ለቅርብ ወዳጅ ዘመዶቹና ለስራ ባልደረቦቹ "ድንገተኛ ችግር አጋጥሞኛል" የሚሉ የሀሰት የገንዘብ ድጋፍ ጥያቄዎችን ይልካሉ። ይህም ድርጊት በማህበረሰቡ መካከል ያለውን መተማመን ከመሸርሸሩ ባለፈ፣ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ በማጭበርበር እንዲመዘበር በማድረግ መጠነ-ሰፊ የኢኮኖሚና የስነ-ልቦና ጉዳት እያደረሰ እንደሚገኝ ነው ተቋሙ ያስታወቀው። ከላይ የተጠቀሱና መሰል የሳይበር ደህንነት ስጋቶችን ለመቀነስ፣ የመንግስትና የግል ተቋማት እንዲሁም ማህበረሰቡ ከመቼውም ጊዜ በላይ ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባ ኢመደአ አሳስቧል። ከማይታወቁ ወይም ካልተረጋገጡ አድራሻዎች በዋትሳፕ፣ በቴሌግራም እና በሌሎች መድረኮች የሚላኩ ሊንኮችን ካለመክፈት ባለፈ፣ አጠራጣሪ መልዕክቶች ሲደርሱ ወዲያውኑ "Report" እና "Block" በማድረግ የጥቃቱን ስርጭት መግታት እንደሚያስፈልግ አስገንዝቧል። በተጨማሪም ማንኛውንም አይነት ሚስጥራዊ የይለፍ ቃል ወይም በስልክ የሚላክ የማረጋገጫ ኮድ (Verification Code) ለማንም አካል አለመስጠት ለዲጂታል ደህንነት ወሳኝ መሆኑን አመልክቷል። አስተዳደሩ እያንዳንዱ ተጠቃሚ በተለይም ማህበረሰቡ በመተግበሪያዎቹ ላይ የሁለትዮሽ ማረጋገጫ (Two-Step Verification) በአስቸኳይ እንዲተገብር መክሯል። ይህ የቴክኖሎጂ የመረጃ ጠላፊዎች የግለሰቦችን አካውንት በቀላሉ እንዳይቆጣጠሩ የሚያደርግ እና ተጨማሪ የደህንነት ቁልፍ የሚፈጥር አስተማማኝ የመከላከያ ዘዴ እንደሆነ ገልጾ ዜጎች ይህንን ቀላል ግን ውጤታማ የሆነ የደህንነት ጥንቃቄ ተግባራዊ በማድረግ፣ ራሳቸውን በቴክኖሎጂ ከታገዙ የማጭበርበር ድርጊቶች ሊታደጉና የሳይበር ወንጀለኞችን ሴራ ሊያከሽፉ እንደሚገባ አስተዳደሩ ያሳሰበው። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር እነዚህን የሳይበር ወንጀለኞች በህግ ተጠያቂ ለማድረግ ከሚመለከታቸው የጸጥታና የፍትህ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቋል። ማህበረሰቡ ማንኛውም የሳይበር ጥቃት ሙከራ ሲያጋጥመው ወይም አጠራጣሪ እንቅስቃሴዎችን ሲመለከት በነጻ ስልክ መስመር 933 በመደወል ለኢመደአ ጥቆማ እንዲሰጥ ጥሪ ቀርቧል። የሳይበር ደህንነትን ማስጠበቅ የአንድ ተቋም ብቻ ሳይሆን የሁላችንም የጋራ ኃላፊነት በመሆኑ፣ የቴክኖሎጂ አጠቃቀማችንን በንቃትና በጥንቃቄ በመምራት የሀገራችንን ሰላምና ደህንነት በጋራ መጠበቅ እንደሚገባም መግለጫው አትቷል።
በአዲስ አበባ ተጨማሪ ዘጠኝ የ"አዲስ መሶብ" የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎችን ወደ ስራ ለማስገባት ዝግጅት እየተደረገ ነው 
Jan 27, 2026 174
አዲስ አበባ፤ ጥር 19/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ተጨማሪ ዘጠኝ የ"አዲስ መሶብ" የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎችን ወደ ስራ ለማስገባት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዮናስ ዓለማየሁ ገለጹ፡፡ ለዜጎች የሚሰጠው አገልግሎት በቴክኖሎጂ የታገዘውን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በፌዴራል ደረጃ፣ በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች እንዲሁም በሁሉም ክልሎች ተደራጅቶ ወደ ስራ መግባቱ ይታወቃል፡፡   የአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዮናስ ዓለማየሁ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ማዕከሉ አገልግሎት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ከ55ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አገልግሎት መስጠት ተችሏል። በማዕከሉ የአገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ በተደረገ የዳሰሳ ጥናት የሚሰጠው አገልግሎት በተገልጋዮች ዘንድ እርካታን እንደፈጠረ ማመልከቱን ጠቁመው፤ ማዕከሉ ሥራ ሲጀምር 107 የነበሩት የአገልግሎት ዓይነቶች አሁን ላይ ወደ 132 ማደጋቸውን አስታውቀዋል። በቅርቡ ተጨማሪ አራት ተቋማት ወደ ማዕከሉ እንደሚገቡ ገልጸው፤ ይህም የአገልግሎት ተደራሽነትን በማስፋት ረገድ ዓይነተኛ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል።   የአገልግሎት ሰጪ ባለሙያዎችም ሥነ-ምግባርን ከቴክኖሎጂ ክህሎት ጋር አጣምረው እንዲሰሩ መደረጉ ለተመዘገበው ውጤት ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅት አገልግሎቱ በዋና መሥሪያ ቤትና በአንድ ቅርንጫፍ ብቻ እየተሰጠ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ ይህንን ተደራሽነት ለማስፋት ዘጠኝ ተጨማሪ ቅርንጫፎችን ለመክፈት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይም በጉለሌ፣ አዲስ ከተማ፣ ቂርቆስና ልደታ ክፍለ ከተሞች አማካይ ቦታዎች ላይ የሚገኙ አራት ቅርንጫፎች የሕንጻ እድሳታቸው እየተጠናቀቀ በመሆኑ በቅድሚያ ወደ ሥራ ይገባሉ ብለዋል፡፡   በቀሪዎቹ አምስት ክፍለ ከተሞችም በተመሳሳይ የአንድ ማዕከል አገልግሎቱን መጀመር የሚያስችሉ የግንባታ ሥራዎች እየተፋጠኑ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። ከአገልግሎት መስፋፋቱ ጎን ለጎን ማዕከላቱን ለተገልጋዮች ይበልጥ ምቹ የማድረግ ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን አቶ ዮናስ ገልጸዋል። ለዚህም ማሳያ እንዲሆን ሕጻናትን ይዘው ለሚመጡ ተገልጋዮች የሕጻናት ማቆያ ከመገንባት ባለፈ፣ ተገልጋዮች የጤና እርዳታ የሚያገኙበት ሥርዓት እየተዘረጋ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም መንጃ ፈቃድ የሚያሳድሱ ተገልጋዮች ለማሽከርከር ብቁ መሆናቸውን የሚያረጋግጥ የጤና ምርመራ አገልግሎትን በዚያው በማዕከሉ እንዲያገኙ ለማስቻል ከከተማዋ ጤና ቢሮ ጋር በትብብር እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
የፋይናንስ ወንጀሎችን ለመከላከል የሰው ሠራሽ አስተውሎትን መሰረት ያደረገ ሥርዓት ሊለማ ነው
Jan 27, 2026 129
አዲስ አበባ፤ ጥር 19/2018 (ኢዜአ)፡- በሕገ-ወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስሎ የመጠቀምና ሽብርተኝነትን በገንዘብ የመርዳት ወንጀሎችን መከላከል የሚያስችል በሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) የታገዘ ሥርዓት ለማልማት ስምምነት ተፈረመ። ስምምነቱን የፈረሙት የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) እና የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሙሉቀን አማረ ናቸው።   የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) በዚህ ወቅት፤ ስምምነቱ የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት በሕገ-ወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስሎ የመጠቀምና ሽብርተኝነትን በገንዘብ የመርዳት ወንጀሎችን ለመከላከል የሚያደረገውን ጥረት ያግዛል ብለዋል፡፡ ሥርዓቱ ሰው ሠራሽ አስተውሎትን መሰረት በማድረግ ረቂቅ ወንጀሎች ከመፈጸማቸው በፊት ማስቀረትና ችግሩ ሲፈጠር የከፋ ጉዳት ሳይደርስ በፍጥነት መፍታት የሚያስችል መሆኑንም አስገንዝበዋል። ይህን ሥርዓት ለማልማት የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን አውስተው፤ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የላቀ ሥራና በተያዘለት ጊዜ ሠርቶ ለማስረከብ ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡   የፋይናንስ ደኅንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሙሉቀን አማረ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የፋይናንስ ተቋማት ኅብረት እና የዓለም አቀፉ የፋይናንስ ድርጊት ግብረ-ኃይል አባል እንደመሆኗ የፋይናንስ ወንጀል መረጃዎችን ከሌሎች ሀገራት ጋር እንደምትለዋወጥ ገልጸዋል፡፡ በዚህም በሕገ-ወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስሎ የመጠቀምና ሽብርተኝነትን በገንዘብ የመርዳት ወንጀሎች ውስብስብና ድንበር ተሻጋሪ በመሆናቸው የቴክኖሎጂ ድጋፍ ያስፈልጋል ነው ያሉት። የሥርዓቱ መልማት ውስብስብ የሆነውን ወንጀል ከሀገራት ጋር በትብብር ብሎም ከሕግ አስከባሪዎች ጋር በጋራ በመሥራት ከወንጀል ማትረፍ እንደማይቻል ለማሳየት እንደሚያግዝ አመላክተዋል። ኢትዮጵያ በሕገ-ወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስሎ የመጠቀምና ሽብርተኝነትን በገንዘብ የመርዳት ወንጀሎችን ለመከላከልና ደኅንነቷን ለማረጋገጥ ሥርዓት ማልማቷ ለብዙ የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ ይሆናል ብለዋል፡፡
የወታደራዊ ቴክኖሎጂ ውጤቶቹ የኢትዮጵያን የሩቅ ዘመን የልዕልና ህልም በተጨባጭ በቅርቡ እንደምናሳካው ማረጋገጫዎች ናቸው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Jan 27, 2026 154
አዲስ አበባ፤ ጥር 19/2018(ኢዜአ)፦ በአየር ኃይል ኤክስፖው የታዩ የወታደራዊ ቴክኖሎጂ ውጤቶች የኢትዮጵያን የሩቅ ዘመን የልዕልና ህልም በተጨባጭ በቅርቡ እንደምናሳካው ማረጋገጫዎች ናቸው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ዓለም አቀፍ የአየር ኃይል ኤክስፖን ዛሬ ጎብኝተዋል።   ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት የኢትዮጵያ አየር ኃይል የ90 ዓመታት ጉዞ በድልና በጀግንነት ብቻ የተገደበ አይደለም፤ በፈጠራና የቴክኖሎጂ ልዕልና ውጤትም ጭምር መሆኑን ተናግረዋል። በአየር ኃይል ዋና መሥሪያ ቤት በተከፈተው ዓለም አቀፍ የአየር ኃይል ኤክስፖ ዛሬ የተመለከትነው እውነትም ይሄንኑ የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል።   በኤክስፖው የተመለከትናቸው የወታደራዊ ቴክኖሎጂ ውጤቶች የኢትዮጵያን የሩቅ ዘመን የልዕልና ህልም በተጨባጭ በቅርቡ እንደምናሳካው ማረጋገጫዎች ናቸው ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት።
የሴቶችን ሳይንሳዊ የፈጠራና ክህሎት አቅም በማበልጸግ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ይሰራል
Jan 26, 2026 137
አዲስ አበባ፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፦ የሴቶችን ሳይንሳዊ የፈጠራ ክህሎት አቅም በማበልጸግ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እንደሚሰራ የስፔስ ሳይንስና ጂኦ ስፓሻል ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ይሽሩን አለማየሁ (ዶ/ር) ገለጹ። በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የሴቶችን አቅም ለማሳደግ ዓላማ ያደረገ የስልጠና መድረክ ከሁሉም የሀገሪቱ ክልሎች ለተውጣጡ የሁለተኛ ደረጃ ሴት ተማሪዎችና የሳይንስ መምህራን እየተሰጠ ይገኛል።   ስልጠናው ለሶስተኛ ጊዜ እየተሰጠ መሆኑ ተገልጿል። በመድረኩ የስፔስ ሳይንስና ጂኦ ስፓሻል ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ይሽሩን አለማየሁ(ዶ/ር)፤ የሴቶች የሳይንስና ቴክኖሎጂ የፈጠራ ክህሎት ለሀገር ሁለንተናዊ ብልጽግና ጉልህ ድርሻ አለው ብለዋል። የሴቶችን ሳይንሳዊ የፈጠራ ክህሎት አቅም በማበልጸግ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራትም አበረታች ውጤት እየተገኘ መሆኑን ገልጸዋል። ስልጠናውም ሴቶች በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላቸውን ዕውቀትና ክህሎት የበለጠ ለማበልጸግ አቅም እንደሚፈጥር አስረድተዋል። በቀጣይም የሴቶችን ሳይንሳዊ የፈጠራና ክህሎት አቅም በማበልጸግ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ ገልፀዋል።   ‎የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ ሶሳይቲ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኪሩቤል መንበሩ በበኩላቸው፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ላይ የሚደረግ ኢንቨስትመንት የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ ጉልህ ፋይዳ አንደሚኖረው ገልጸዋል። የስልጠናው ተሳታፊ ሴቶችም የሚያገኙትን ዕውቀትና ክህሎት በማበልጸግ የሳይንስና ቴክኖሎጂ የፈጠራ አቅማቸውን ማሳደግ እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል። ‎ከስልጠናው ተሳታፊዎች መካከል አዳነች አለሙ ስልጠናው በቀጣይ በዘርፉ ለሚኖራቸው የፈጠራ ስራ እና እውቀት መሰረት የሚጥል መሆኑን ገልጸዋል። በዘርፉ የሚያገኙት አዲስ እውቀትም ለተማሪዎቻቸው ለማስገንዘብ እድል ይፈጥርልናል ያሉት ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ፋጡማ መሀመድ ናቸው።  
ኢኒስቲትዩቱ ይፋ ያደረገው የእንሰት መፋቂያ ቴክኖሎጂ የሥራ ጫናን ከማቅለል ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጥሯል
Jan 24, 2026 139
ሀዋሳ፤ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፦የባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ከአርባ ምንጭ ዩኒቨርስቲ ጋር በመቀናጀት ይፋ ያደረገው የእንሰት መፋቂያ ቴክኖሎጂ የሥራ ጫናን ከማቃለል ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሀብት ልማት፣ሥራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። የቋሚ ኮሚቴው አባላት በሲዳማ ክልል ደቡባዊ ሲዳማ ዞን አለታ ወንዶ ወረዳ በኢንስቲትዩቱ የተሰራ ዘመናዊ የእንሰት መፋቂያ ቴክኖሎጂ ሽግግር ስራን ተመልክተዋል። የቋሚ ኮሚቴው ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሺ ሀሰን በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፣ኢንስቲትዩቱ የህብረተሰቡን ኑሮ የሚያቃልሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እያፈለቀ ይገኛል።   ከእነዚህ ውስጥ በሴቶች ላይ የሚደርሰውን የስራ ጫና የሚያቃልል የእንሰት መፋቂያ፣ መጭመቂያና መቁረጫ መሳሪያ አንዱ ነው ብለዋል። በርካታ ሴቶች በእንሰት ሥራ እንደሚሰማሩ ገልጸው፣ እንዲህ አይነት ቴክኖሎጂዎች መምጣታቸው የሥራ ጫናውን ከማቃለል ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል የሚፈጥር ነው ብለዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የኢትዮጵያ አየር ኃይል ፈጣን እድገት ለአፍሪካ ሀገራት አብነት ይሆናል - የአፍሪካ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች
Jan 23, 2026 213
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር ኃይል ፈጣን እድገት ለአፍሪካ ሀገራት አብነት ይሆናል ሲሉ የአፍሪካ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት ክብረ በዓልን በማስመልከት የተዘጋጀው የአቪዬሽን ኤክስፖ ተከፍቷል።   ኤክስፖው የወደፊቱን የአቪዬሽን አቅም በጋራ እንገንባ በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ ሲሆን፤ ኤክስፖውን የጎበኙ የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች፤ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ለአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ በሚሆን አግባብ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ ስለመሆኑ መታዘባቸውን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የቦትስዋና ኤምባሲ ወታደራዊ አታሼ ኮሎኔል ሞታሲ ቼሌኒያኔ፤ የኢትዮጵያ አየር ሃይል በአቪዬሽን፣ ኢንጂነሪንግና ቴክኖሎጂ ዘርፍ አስደማሚ ለውጥ ውስጥ መሆኑን ከኤክስፖው መመልከታቸውን ገልጸዋል።   በተለይ አየር ኃይሉን ጥገናን ጨምሮ በሌሎች ቁልፍ የዘርፉ ምህንድስና ስራዎች ራሱን ለመቻል እያከናወነ ያለው ስራ የሚደነቅ መሆኑን አንስተው፤ በርካታ የአፍሪካ ሀገራት ከዚህ ልምድ መውሰድ እንዳለባቸው ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የናሚቢያ ኤምባሲ ወታደራዊ አታሼ ማካንዚ ቺቤራ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ ባለፉት ጊዜያትም ሆነ አሁን ላይ የኢትዮጵያ አየር ኃይል የራሱን እና የአፍሪካን አቅም ለማሳደግ ጥረት እያደረገ ነው።   የአፍሪካ ሀገራት በጋራ እና በትብብር ከሰሩ ብዙ ርቀት መሄድ እንደሚችሉ ጠቁመው፤ በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ አየር ሃይል የወሰደውን ተነሳሽነት አድንቀዋል።   በኢትዮጵያ የጋቦን ኤምባሲ ወታደራዊ አታሼ ኮሎኔል አርሲዴ አንጉሌ፤ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ሀገር የሚወክል ተቋም እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል። ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ጥሩ ምሳሌ ነው ብለዋል።
የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ሥራችንን ለማዘመንና ለማቀላጠፍ አግዞናል -ሰልጣኞች
Jan 23, 2026 227
ወልቂጤ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮ-ኮደርስ ያገኙት ስልጠና የዲጂታል ክህሎታቸውን በማሳደግ ሥራቸውን ለማዘመንና ለማቀላጠፍ እንዳገዛቸው በወልቂጤ ከተማ የኮደርስ ሰልጣኞች ገለጹ። መንግስት ለዜጎች ያመቻቸው የአምስት ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና ዜጎች ከዲጂታል ዓለሙ ጋር ለመራመድ የሚያስችላቸውን የቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት እያስጨበጣቸው ነው። በወልቂጤ ከተማ አስተዳደር በተለያዩ ተቋማት የሚሰሩ ሠራተኞችም ስልጠናውን እንዲወስዱ በአስተዳደሩ የተመቻቸላቸውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም የዲጂታል እውቀታቸውን እያሳደጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። ስልጠናውን የወሰዱት ሠራተኞች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በኢትዮ-ኮደርስ በተለያዩ ዘርፎች ያገኙት ስልጠና የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማሳደግ ሥራቸውን እንዲያዘምኑና ውጤታማ እንዲሆኑ እያገዛቸው ነው።   በወልቂጤ ከተማ የኢንተርፕራይዝና ሥራ ዕድል ፈጠራ ጽህፈት ቤት ባለሙያ ወጣት ሰለሞን ደርብ በኢትዮ ኮደርስ በዳታ ፕሮግራሚንግ፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎትና በአንድሮይድ ዘርፎች ስልጠና ወስዶ ክህሎቱን ማሳደጉን ተናግሯል፡፡ በአሁኑ ወቅትም በሌሎች ዘርፎች ተጨማሪ ስልጠና እየወሰደ መሆኑን ጠቁሞ፣ በኮደርስ ስልጠና ባገኘው እውቀት በትርፍ ሰአቱ ተጨማሪ ሥራ ለመፍጠር እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ተናግሯል። የከተማው ሳይንስ እና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት ባለሙያ ወጣት ጅብሪል መጀል በበኩሉ፤ የዲጂታል እውቀቱን ለማሳደግ የሚያግዘውን የኮደርስ ስልጠና በመውሰድ ከራሱ ባለፈ ሌሎችን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ተናግሯል።   ያገኘው ስልጠና በኮምፒውተር ሳይንስ በዲግሪ ለመማር መነሳሳት እንደፈጠረለት ገልጾ፣ በቀጣይም በተለያዩ ዘርፎች የሚሰጠውን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዱን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጿል። በማይክሮ ሶፍት መተግበሪያዎች በወሰደው ስልጠና ያገኘውን እውቀትና ክህሎት በተቋም ሥራ በመተግበር ሥራውን ለማቀላጠፍና ለችግር መፍቻነት እየተጠቀመበት መሆኑን ተናግሯል። በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዲጂታል ቴክኖሎጂ ያለንን እውቀትና ክህሎት በማሳደግ ከዲጂታል ዓለም ፈጣን እድገት ጋር ለመጓዝ የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ ሌላኛዋ ሰልጣኝ ወይዘሮ አቻምየለሽ ዘርጋ ናቸው።   ስልጠናው ከኋላቀር የመረጃ አያያዝ ስርዓት በማላቀቅ የግልና የመስሪያ ቤት መረጃዎችን ለማዘመን የሚያስችል እውቀት እንዳገኙበት ተናግረዋል፡፡ በኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና በአራት የተለያዩ ዘርፎች የቀሰሙት እውቀት በቴክኖሎጂ ብቁና ተወዳዳሪ ባለሙያ እንዳደረጋቸው የተናገሩት ደግሞ የከተማው ንግድና ገበያ ልማት ባለሙያ አቶ ጅላሉ ሙዘይን ናቸው ። ስልጠናው የተለያዩ አገልግሎት የሚሠጡ ሶፍትዌሮችን አበልጽገው እንዲጠቀሙ እድል መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡   የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሃምዱ ካሚል፤ በከተማው እስካሁን ድረስ 20ሺህ የሚጠጉ ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስደው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። በቀጣይ ስልጠናውን በሁሉም የመንግስት መዋቅር ተደራሽ በማድረግ ዜጎች የቴክኖሎጂ ክህሎትና ዕውቀታቸውን ለማሳደግ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።
ኮሌጆች ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት  የማይተካ ድርሻ አላቸው
Jan 23, 2026 142
ቦንጋ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት በሚደረገው ርብርብ ብቃት ያለው የሰው ሀይል በማፍራት የማይተካ ድርሻ እንዳላቸው የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በቦንጋ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ኢትዮ ኮደርስ ስልጠናና ፋይዳ መታወቂያን ተደራሽ ለማድረግ ያለመ የንቅናቄ መድረክ አካሂዷል።   በመድረኩ የተገኙት የቢሮ ምክትል ሀላፊና የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ዘርፍ ሀላፊ አቶ ምትኩ አስፋው እንደገለጹት፤ ኮሌጆች ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት በሚደረገው ርብርብ ብቃት ያለው የሰው ሀይል በማፍራት የማይተካ ሚና አላቸው፡፡ ለዚህም ራሳቸውን በቴክኖሎጂ ግብአቶች በማደራጀት ለሰው ሀይል ልማት ትኩረት መስጠት እንዳለባቸው አክለዋል። ለዲጂታል ኢትዮጵያ መሳካት ድርሻ ላላቸው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እና ለፋይዳ መታወቂያ ኢንሼቲቮች ትኩረት መስጠት ሌላው ተግባራቸው መሆን እንዳለበትም አስገንዝበዋል። በክልሉ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዓመት ከ110 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ እስካሁን ድረስ 28 ሺህ 90 ሰዎች እንደወሰዱና 8 ሺህ የሚጠጉትም ሰርተፊኬት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ዜጎችን የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ ከማድረግ አንጻር በዓመቱ ለማሳካት ከታቀደው ውስጥ እስካሁን ድረስ 246 ሺህ 436 ዜጎችን የመታወቂያው ባለቤት ለማድረግ መቻሉንም ጠቁመዋል። ሥራውን ለማሳካትም የአሁኑ የንቅናቄ መድረክ ተደማሪ አቅም ይሆናል ብለዋል።   በመድረኩ የተገኙት የካፋ ዞን ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን መምሪያ ሀላፊ አቶ ተፈሪ ታደሰ በበኩላቸው፤ በዞኑ በኮደርስ ስልጠና በፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ሥራዎች እንደተጀመሩና ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። ኢንሼቲቮቹን ለማሳካት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ከሁለተኛ እና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ጋር በቅንጅት እንዲሰሩ መደረጉንም ጠቁመዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የትምህርት ጥራትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ አጋዥ ሚና ይኖረዋል   
Jan 23, 2026 118
አክሱም ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትግበራ የትምህርት ጥራትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ አጋዥ ሚና እንደሚኖረው የአክሱም ከተማ መምህራን ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ ቀጣይ 5 ዓመታት የዲጂታል ጉዞ የሚመራበትን ''ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ'' በቅርቡ ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል። ዲጂታል ቴክኖሎጂ የሰውን ልጅ የመፈጸም አቅም በማሳደግና የሀገርን ልማት በማሳለጥ ረገድ ቁልፍ ሚና ይጫወታል። በኢትዮጵያ የትምህርት ጥራት ሥብራትን ለመጠገን እየተደረገ ያለውን ጥረት ውጤታማ ለማድረግ የቴክኖሎጂ ተደረሽነትን ማስፋት ቁልፍ ጉዳይ ነው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአክሱም ከተማ መምህራንም በዚህ ሀሳብ ይስማማሉ።   በአክሱም የአልሙናይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህር ያሬድ መኮንን፣ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥና ተማሪዎችን በቂ ዕውቀት ለማስጨበጥ ከፍተኛ እገዛ ያደርጋል ብለዋል። የፈተና አሰጣጡ በዲጂታል ቴክኖሎጂ መታገዙም ኩረጃን የሚያስቀርና የፈተና ደህንነትን የሚያስጠብቅ መሆኑንም ነው ያመለከቱት። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትግበራ የትምህርት ጥራትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ አጋዥ ሚና እንደሚኖረው በመግለጽ። መምህር ሙዑዝ በየነ በበኩላቸው፣ የዲጂታል 2030 ስትራቴጂ ትግበራ ተማሪዎች ተግባር ተኮር ዕውቀትና ክህሎት እንዲያዳብሩ ያግዛል ብለዋል።   የመማር ማስተማር ሂደቱን ፈጣንና ቀልጣፋ ከማድረግ ባለፈ የትምህርት ተደራሽነትን ለማስፋት ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ ስትራቴጂው ተማሪዎች አጋዥ መጽሐፍትን በቀላሉ እንዲያገኙና የዕውቀት አድማሳቸውን እንዲያሰፉ ቁልፍ ሚና ይጫወታል ያሉት ደግሞ መምህር ግደይ ካሓሱ ናቸው።   በትምህርት ጥራት ላይ ይነሳ የነበረውን ተደጋጋሚ ቅሬታ ለመፍታትም ከፈተና አወጣጥ ጀምሮ ያለውን ሂደት ግልጽና ተጠያቂነት የሰፈነበት እንዲሆን ያግዛል ነው ያሉት።
ባዮ ጋዝ በመጠቀማችን ጤንነታችንን መጠበቅ ችለናል- አርሶ አደሮች 
Jan 23, 2026 120
ጎንደር ፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ)፡- ባዮ ጋዝ መጠቀም በመቻላቸው ከሚያገኙት ጥቅም በሻገር ጤንነታቸውን ለመጠበቅ እንዳገዛቸው የማእከላዊ ጎንደር ዞን አርሶ አደሮች ተናገሩ፡ በዞኑ ዘንድሮው ዓመት 180 የባዮ ጋዝ ማብላያዎች የግንባታ ስራ እየተከናወነ መሆኑ ተመልክቷል። በማእከላዊ ጎንደር ዞን የምእራብ በለሳ ወረዳ ነዋሪ አቶ መኳንንት የአብስራ ለኢዜአ እንደገለጹት፤የባዮ ጋዝ ማብላያ በመገንባት ላለፉት ሶስት ዓመታት ለምግብ ማብሰልና ለመብራት እየተጠቀሙ ይገኛሉ። ይህም ቀደም ሲል ለምግብ ማብሰያና ለመብራት አገልግሎት ማገዶን በመጠቀም ጭሱ በጤናቸው ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ለመቀነስና ለሀይል አቅርቦት ይጨፈጭፍ የነበረን ደን ለመጠበቅ እንደቻሉ ገልጸዋል።   የባዮ ጋዙ ለኃይል አቅርቦት ከመዋሉም ባሻገር ተረፈ ምርቱን ለመሬታቸው የተፈጥሮ ማዳበሪያ በመጠቀም ምርታማነታቸውን ማሳደግ መቻላቸውን የገለጹት ደግሞ የወገራ ወረዳ ነዋሪ አርሶአደር በላይ ቸርነት ናቸው፡፡ የባዮ ጋዝ ሃይል አቅርቦቱ ለአጠቃቀም ቀላልና ልጆቻቸው ትምህርታቸውን በማታ ለማጥናት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል።፡ በጎንደር ዙሪያ ወረዳ የምንዝሮ ቀበሌ ነዋሪ አርሶአደር ተሾመ ንጉሴ በበኩላቸው የባዮ ጋዝ ቴክኖሎጂ ሴቶችና ህጻናትን ማገዶ ፍለጋ ይደርስባቸውን የነበረውን መንከራተት ያስቀረ ነው ብለዋል፡፡ በማእከላዊ ጎንደር ውሃና ኢነርጂ መምሪያ የፕላንና ፕሮግራም ቡድን መሪ አቶ ማሩ ታደሰ እንደገለጹት፤ በዘንድሮ ዓመት በ13 ወረዳዎች 180 የባዮ ጋዝ ማብለያዎች ግንባታ ለማከናወን እየተሰራ ነው።   እስካሁንም ተጠቃሚ አርሶ አደሮችን መለየት፣ የኢንዱስትሪ ውጤቶችን የማቅረብና አርሶ አደሩ እንደ አሸዋና ድንጋይ ያሉ የአካባቢ ቁሳቁሶችን እንዲያቀርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። የባዮ ጋዝ ማብለያዎቹን ግንባታ በዚህ ዓመት መጨረሻ ሙሉ በሙሉ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት በማብቃት አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
በዩኒቨርሲቲው የተለያዩ ጥናታዊ ጽሁፎችን ጨምሮ ከ400ሺህ በላይ መጽሐፍት በዲጂታል ሥርዓት ተደራጅተዋል
Jan 23, 2026 100
ጎንደር፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎችን ጨምሮ ከ400ሺህ በላይ መጽሐፍት በዲጂታል ሥርዓት መደራጀታቸውን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት አሥራት አፀደወይን(ዶ/ር) ገለጹ። ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በየዓመቱ የሚያዘጋጀው የመጽሐፍት ዐውደ ርዕይ ''መጽሐፍት ለንባብ፣ ንባብ ለዕውቀት፣ ዕውቀት ለህይወት'' በሚል መሪ ሃሳብ ትናንት ተጀምሯል።   የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት አሥራት አፀደወይን(ዶ/ር) በዐውደ ርዕዩ መክፈቻ ባደረጉት ንግግር የወጣቱን የንባብ ባህል ለማሳደግ አዳዲስ አሰራሮች ተግባራዊ እየተደረጉ ነው ብለዋል። ዲጂታል ቤተ-መጽሐፍትን ማስፋፋትና መጽሐፍትን ዲጂታላይዝድ ማድረግ ንባብን ለማበረታታትና አንባቢ ትውልድ ለመፍጠር ወሳኝ ሚና አለው ብለዋል። ከዚህ አኳያ ዩኒቨርሲቲው የዲጂታል ቤተ-መጽሐፍት በማቋቋምና ጥናታዊ ጽሁፎችና የተለያዩ መጽሐፍትን በዲጂታል ሥርዓት በማደራጀት አንባቢ ትውልድ አንዲፈጠር የድርሻውን እየተወጣ ነው ብለዋል።   እስካሁንም ከ400ሺህ በላይ የታሪክ፣ የሳይንስና የምርምር መጽሐፍትን ጨምሮ ከ10ሺህ በላይ የጥናት ውጤቶችን ወደ ዲጂታል በመቀየር ለተማሪዎች በቀላሉ ተደራሽ ማድረግ መቻሉን አንስተዋል።   የኢትዮጵያ ደራሲያን ማሕበር ፕሬዝዳንት የዝና ወርቁ በበኩላቸው፣ በኢትዮጵያ የንባብ ባህልን ለማሳደግ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሚና የጎላ ነው ብለዋል። ተቋማቱ ወጣቱ መጽሐፍትን በቀላሉ ማግኘት የሚችልባቸው ዲጂታል አሰራሮች ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባቸውም አንስተዋል። ለአንድ ሳምንት በሚቆየው የመጽሐፍት ዐውደ ርዕይ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ ደራሲያን፣ አሳታሚዎችና መጽሐፍት አከፋፋዮች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከዲጂታል ዓለም ጋር ለመተዋወቅ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Jan 22, 2026 164
ወላይታ ሶዶ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከዲጂታል ዓለም ጋር ይበልጥ ለመተዋወቅና በዘርፉ የራሳቸውን ሥራ ፈጥረው ለመንቀሳቀስ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው የወላይታ ሶዶ ከተማ ሰልጣኞች ተናገሩ። መንግስት በመላው ኢትዮጵያ ለአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን የኮደርስ ስልጠና ለመስጠት ግብ ጥሎ እየሰራ ነው። በወላይታ ሶዶ ከተማም 18 ሺህ 400 ዜጎችን በኢትዮ ኮደርስ ለማሰልጠን እየተሰራ ይገኛል። የኮደርስ ስልጠና የወሰዱ የከተማዋ ነዋሪዎች ስልጠናው ከዲጂታል ዓለም ጋር ይበልጥ እንዲተዋወቁና የራሳቸውን ሥራ በመፍጠር ተጠቃሚ ለመሆን ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት ሰልጣኞች መካከል አቶ ደምሴ አሻ፤ በኮደርስ በተለያዩ ዘርፎች የወሰዷቸው ስልጠናዎች የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማሳደግ በዲጂታል ዓለም እኩል ለመንቀሳቀስ የሚያስችል ክህሎት እንዳስጨበጧቸው ገልጸዋል።   በአሁኑ ወቅትም ባገኙት እውቀት የራሳቸውን ሥራ ፈጥረው እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ገልጸው፣ በተጨማሪም በተለያዩ ተቋማት ያሉ ሠራተኞችን በማሰልጠን ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መምጣታቸውን ተናግረዋል። ስልጠናው በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ ያለኝን እውቀት አሳድጎልኛል ያሉት ደግሞ ሒሩት አርጃ ናቸው።   በኢትዮ ኮደርስ የፕሮግራሚንግ ስልጠና መውሰዳቸውንና በአሁኑ ወቅት በሰውሰራሽ አስተውሎት ስልጠናቸውን እየተከታተሉ መሆናቸውን ገልጸው፣ ከስልጠናው ዲጂታል ዓለምን የሚመጥን እውቀት መቅሰማቸውን ተናግረዋል። ስልጠናው የኮምፒውተርና የዲጂታል እውቀቴን በማሳደግ ከዓለም ጋር ይበልጥ የምቀራረብበትን ዕድል ሰጥቶኛል ያሉት ደግሞ አቶ ሙሉጌታ ዶላ ናቸው።   በስልጠናው ያገኙት እውቀት በዲጂታል ዓለም ተወዳዳሪ እንደሚያደርጋቸው ተናግረው፣ ያገኙት እውቀት ከተቋማዊ አሰራር ጋር በማስተሳሰር ውጤታማ ሥራ ለማከናወን እንዳስቻላቸውም ገልጸዋል። የወላይታ ሶዶ ከተማ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ ተሻለ ታደሰ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ መምሪያው ስልጠናውን ተደራሽ በማድረግ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተጀመረውን ሥራ ለማገዝ እየሰራ ነው።   የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከተጀመረ ወዲህ በከተማው ከ10 ሺህ በላይ ሰዎች ስልጠናቸውን አጠናቅቀው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ገልጸው፣ ከነዚህ ውስጥ 3ሺህ 480 የሚሆኑት ባለፉት ስድስት ወራት ስልጠናውን የወሰዱ ናቸው ብለዋል። በተያዘው ዓመት ዕቅዱን ለማሳካትም የአንድ ጀንበር ምዝገባ ንቅናቄ በማካሄድና በሁሉም አካባቢዎች ያሉ ዜጎችን ለማሰልጠን በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ‎ስልጠናው በዲጂታል ክህሎት የዳበረ ማህበረሰብ ለመፍጠርና የዲጂታል ዓለምን በፍጥነት የሚላመድ ትውልድ ለማፍራት የጎላ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል።
በአፋር ክልል 2 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዓመት ዕድሜ ያለው "ፓራንትሮፐስ" የተሰኘ የሰው ዘር ቅሪተ አካል ተገኘ
Jan 21, 2026 236
አዲስ አበባ፤ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ አፋር ክልል ሚሌ-ሎጊያ ፓሊዮአንትሮፖሎጂ መካነ ቅርስ ስፍራ 2 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዓመት ዕድሜ ያለው "ፓራንትሮፐስ" የተሰኘ የሰው ዘር ቅሪተ አካል መገኘቱ ተገለጸ። በአፋር ክልል ሚሌ-ሎጊያ የፓሊዮአንትሮፖሎጂ መካነ ቅርስ ስፍራ የተገኘው ቅሬተ አካሉም ከዚህ ቀደም ተገኝቶ የማያውቅ የቅድመ ሰው ዘር መሆኑ ተመላክቷል። የቅድመ ሰው ዘር ቅሪተ አካሉን ለማግኘት በአሜሪካ ቺካጎ ዩኒቨርስቲ የዘርፉ ተመራማሪ ፕሮፌሰር ዘረሰናይ ዓለምሰገድ የተመራ ቡድን ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርጓል። የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኤሊያስ ሽኩር፤ የሀገር ውስጥና የውጭ ተመራማሪዎች የምርምር ውጤቶች የኢትዮጵያን የሰው ዘር መገኛነት የሚያጠናክሩ ናቸው ብለዋል።   በኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የበርካታ ቅድመ ሰው ዝርያ ቅሪተ አካል ግኝቶችም የዓለምን ማህበረሰብና ተመራማሪዎችን ቀልብ እየሳበ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የፕሮፌሰር ዘረሰናይ ዓለምሰገድ የጥናት ቡድን በአፋር ክልል ያገኘው ፓራንትሮፐስ የተሰኘ የቅድመ ሰው ዘር ቅሪተ አካልም የኢትዮጵያን የሰው ዘር መገኛነት ዳግም ያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የቅድመ የሰው ዘር መገኛነት የጥናት ውጤት ማረጋገጫዎችም በቱሪዝም ዘርፍና በዲፕሎማሲ እንቅስቃሴ ጉልህ ሚና እንደሚጫወት አንስተዋል። ኢትዮጵያ ለቅድመ ሰው ዘር ቅሪት አካል ፍለጋና ለሰው ዘር አመጣጥ ጥናት ያላትን ልዩ ጠቀሜታ አጉልቶ እንደሚያሳይ አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ወጣት ተመራማሪዎች በዘርፉ የሚኖራቸውን የላቀ የጥናትና ምርምር ሚና ለማሳደግም ምቹ ሁኔታ የመፍጠር ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል። ለዚህም ብቃት ያላቸው የኢትዮጵያ አንትሮፖሎጂ ተመራማሪዎችን ለማፍራት ከውጭ የዘርፉ ሙያተኞች ጋር በቅርበት እንደሚሰራም ጠቁመዋል። የጥናት ቡድኑ መሪ ፕሮፌሰር ዘረሰናይ ዓለምሰገድ በበኩላቸው፤ ፓራንትሮፐስ የቅድመ ሰው ዘር ከ2 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዓመታት በፊት የኖረ የነበረ የሰው ዝርያ መሆኑን የጥናት ውጤቶቹ እንደሚያሳዩ አረጋግጠዋል። የቅድመ ሰው ዝርያው የተሻለ አካባቢን የመላመድ ባህሪ ያለው በመሆኑ በርካታ አካባቢዎች ላይ መኖሩን የሚያሳዩ የጥናት ውጤቶች እንደተገኙም አስታውቀዋል።
በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የተያዙ ግቦችን እውን ለማድረግ ለሰው ኃይል ልማት ትኩረት ተሰጥቷል
Jan 21, 2026 132
ሀዋሳ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦የብልጽግና ፓርቲ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የተያዙ ግቦችን እውን ለማድረግ የሰው ኃይል ልማት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አስታወቀ። ለብልጽግና ፓርቲ ዋናና ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት አመራሮችና ባለሙያዎች በተቀናጀ የተቋም ሀብት አስተዳደር ትግበራ ላይ ያተኮረ ስልጠና መስጠት ተጀምሯል።   በሥልጠናው መክፈቻ ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል ሥራ፣ ክህሎትና ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክር ቤት አባል ሀገረፅዮን አበበ እንደገለጹት፣ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የተያዙ ግቦች እንዲሳኩ በፓርቲው ለሰው ኃይል ግንባት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።   በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በቴክኖሎጂ የተደገፈ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት፣ ምቹ የአሰራር ሥርዓቶችን በመዘርጋትና የሰው ኃይሉን በማብቃት ረገድ ውጤታማ ሥራ መሰራቱንም አስታውሰዋል። በተጨማሪም አሰራሮችን በቴክኖሎጂ በማዘመን ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት የተያዘው ግብ እንዲሳካም ፓርቲው ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተ መሆኑን ነው የገለጹት። ሥልጠናው በየደረጃው ባሉ የፓርቲው መዋቅሮች ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል መሆኑንም ጠቁመዋል። በብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የስትራቴጂክ ሥራ አመራርና ኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ ዋና ባለሙያ ጌትነት ሙላት በበኩላቸው፣ ስልጠናው በየደረጃው ያሉ የፓርቲው መዋቅሮች ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ወጥ የአሰራር ሥርዓትን እንዲዘረጉ ያግዛል ብለዋል።   በየመዋቅሩ የሰው ኃይል፣ የግዥና ንብረት እንዲሁም የፋይናንስ አስተዳደርና ሌሎች ቁልፍ ተግባራትን በቴክኖሎጂ ታግዞ መስራት ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት የሚደረገውን ጥረት እንደሚያግዝ አንስተዋል። ፓርቲው ለሰው ኃይልና ጠንካራ ተቋም ግንባታ የሰጠውን ትኩረት መሠረት በማድረግ በክልሉ ሰፋፊ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በፓርቲው የሲዳማ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ስትራቴጂክ ሥራ አመራርና ኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ ኃላፊ ታምሩ ዩቴ ናቸው።   ሥልጠናው ተቋማትን በማዘመንና የሰው ኃይልን በማብቃት ወጥና ቀልጣፋ ዲጂታል ሥርዓት ለመገንባት ምቹ አጋጣሚ ይፈጥራል ብለዋል። ዛሬን ጨምሮ ለአራት ቀናት በሚቆየው ስልጠና ከፓርቲው ዋናና ከቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች የተውጣጡ አመራሮችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡
የኮደርስ ስልጠና በዘርፉ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ነው
Jan 21, 2026 150
‎‎‎‎‎‎‎ዲላ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦ የኮደርስ ስልጠና ጥልቅ እውቀት በማስጨበጥ በዘርፉ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ነው ሲሉ የኮደርስ ሰልጣኞች ተናገሩ። በጌዴኦ ዞንና ዲላ ከተማ የስልጠናው ተሳታፊዎችና አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ባለሙያዎች፤የኮደርስ ስልጠና ጥልቅ እውቀት በማስጨበጥ በዘርፉ በዓለም ደረጃ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የስልጠና ዕድሉ ማንም ሊያመልጠው አይገባም ያሉት ሰልጣኞቹ፣ ስልጠናው ያላቸውን የቴክኖሎጂ እውቀት ከማሳደግ ባለፈ ስራቸውን በውጤታማነት ለማከናወን ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል።   በዞኑ የፋይናንስና ፕላን ልማት መምሪያ ባለሙያ አቶ ዳዊት ተፈራ፤ ከዚህ ቀደም በኢትዮ ኮደርስ በዳታ ፕሮግራሚንግ፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎትና በአንድሮይድ ዘርፎች የወሰዱት ስልጠና በዘርፉ የነበራቸውን ክህሎት እንዳሳደገው ተናግረዋል፡፡ በተለይ የዳታ ፕሮግራሚንግ ስልጠና ከተሰማሩበት የሥራ መስክ ጋር በእጅጉ የተቆራኘ በመሆኑ የመፈጸም አቅማቸውን እንዳሻሻለው ነው የገለጹት።   በአሁኑ ወቅትም በፕሮግራሚንግ ዘርፍ ተጨማሪ ስልጠና እየወሰዱ መሆኑን ጠቁመው፣ ይህም እውቀታቸውን በማስፋት ተወዳዳሪነታቸውን እንደሚያሳድገው ተናግረዋል። ከዲጂታል ዓለም ፈጣን እድገት ጋር አብሮ ለመጓዝ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰድ ጠቀሜታ አለው ያሉት የዞኑ ሥራና ክህሎት መምሪያ ባለሙያ አቶ ሰለሞን አበበ ናቸው።   ከዚህ ቀደም በዳታ ፕሮግራሚንግ ዘርፍ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸው በማይክሮ ሶፍት ሁሉም መተግበሪያዎች ላይ ያላቸውን ክህሎት አሳድጎላቸዋል። በተለይ መረጃ አያያዛቸውን በማዘመን ምቹ የሥራ አካባቢ መፍጠር መቻላቸውን ጠቅሰው በሌሎች ዘርፎችም አቅማቸውን ለማሳደግ የኮደርስ ስልጠና መጀመራቸውን ገልጸዋል። ስልጠናው ለቴክኖሎጂ ያለኝን ዝንባሌ ለማጎልበት መልካም አጋጣሚ ፈጥሮልኛል ያለችው ደግሞ የዲላ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ12 ክፍል ተማሪ መድሀኒት ተገኝ ናት።   የጌዴኦ ዞን ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ ደረጀ ሾንጣ እንዳሉት፤ በዞኑ ከ16 ሺህ በላይ ዜጎች ስልጠናውን ተከታትለው በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት አግኝተዋል፡፡ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዘርፉ ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋ ለማፍራት የሚደረገውን ጥረት እያገዘ መሆኑን ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅትም በ80 ማዕከላት በዘመቻ እየተሰጠ ባለው ስልጠናም ከ22 ሺህ በላይ ዜጎች እየተሳተፉ መሆናቸውን ተናግረዋል።   ‎በዲላ ከተማ እየተሰጠ ያለውን ስልጠና የመንግስት ሠራተኞችና አመራሮች፣ መምህራንና ተማሪዎች እየወሰዱ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የዲላ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ ፀሐይ ቦጋለ ናቸው። በዞኑና በዲላ ከተማ አስተዳደር በአንድ ጀንበር ንቅናቄ ከ34 ሺህ በላይ ዜጎች በ93 ማዕከላት የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እየወሰዱ መሆኑ ተመላክቷል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም