ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ አሰራር ቀደም ሲል የነበረውን ውጣ ውረድ ያስቀረ ነው-ተገልጋዮች
Jun 14, 2026 115
ባህር ዳር፤ሰኔ 7/2018 (ኢዜአ)፦ የባህር ዳር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ አሰራር ቀደም ሲል የነበረውን ውጣ ውረድ ያስቀረ ነው ሲሉ በከተማዋ የአገልግሎት አሰጣጡ ተጠቃሚዎች ገለጹ። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነት በመንግስት ተቋማት የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መፍታት ማስቻሉንም ጠቅሰዋል። ተገልጋዮቹ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት አገልግሎቱ የመንግስት ተቋማትን የመረጃ አያያዝ በማዘመን ቀልጣፋ አሰራርን ገቢራዊ በማድረግ ብልሹ አሰራር ማስቀረቱን ገልጸዋል።   አስተያየታቸውን ከሰጡ የባህር ዳር ከተማ ባለጉዳዮች መካከል አቶ ተቀባ ሙሉጌታ እንዳሉት፤ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ አሰራር ቀደም ሲል የነበረውን ውጣ ውረድ ያስቀረ ነው። የንብረት ስም ዝውውር አገልግሎት ለማግኘት መጥተው ጉዳያቸውን በ15 ደቂቃ ውስጥ በተሟላ ሁኔታ ለማጠናቀቅ መቻላቸውን ገልፀዋል። አሰራሩ ቀደም ሲል አንድን ጉዳይ ለማስፈጸም ወደተለያዩ ተቋማት በመመላለስ የሚፈጠርን እንግልትና የጊዜ መባከን ለማስቀረት መቻሉን አስረድተዋል።   በቴክኖሎጂ የተደራጀው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከዚህ ቀደም ሁለትና ሦስት ወራት ይፈጅ የነበረውን ጉዳይ በደቂቃዎች በመጨረስ ፈጣን ምላሽን እየሰጠ ነው ያሉት ደግሞ ሌላው ተገልጋይ አቶ መንግስቴ ጌጡ ናቸው። አገልግሎት አሰጣጡ የህዝብን እርካታ ያረጋገጠ በመሆኑ የመጡበትን የመንጃ ፈቃድ እድሳት አገልግሎት በፍጥነትና ተገቢ ሁኔታ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። አገልግሎቱን ከብልሹ አሰራር በጸዳና በአጠረ ጊዜ በማግኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል።   ሌላዋ ተገልጋይ ወይዘሮ ፍሬህይወት ወርቁ በበኩላቸው የማዕከሉ ዘመናዊ የደንበኞች አገልግሎት ይበልጥ ሊስፋፋ እንደሚገባ አመልክተዋል። የባህር ዳር ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አስተባባሪ አቶ ማስረሻ ፈንታ በበኩላቸው፤ አስተዳደሩ የህዝብ አቤቱታ የሚበዛባቸውን 87 አገልግሎቶች በ13 ተቋማት በማደራጀት የተገልጋይን ፍላጎት ለማሟላት መሰራቱን አስረድተዋል።   ማእከሉ ወደ ስራ ከገባ በኋላም የተገልጋዮች እርካታን ለማሳደግና ብልሹ አሰራርን ለማስወገድ እንደቻለ ጠቁመው ይህም ባለፉት ወራት ከ58 ሺህ በላይ ደንበኞችን ማገልገሉን ጠቅሰዋል። የአገልግሎት አሰጣጡን በየጊዜው በማጥናት አሰራሩን በቴክኖሎጂ የታገዘና ቀልጣፋ በማድረግም የህዝብን እርካታ ከ98 በመቶ በላይ ማድረስ መቻሉን አብራርተዋል። በማዕከሉ ከሚሰጠው አገልግሎት በተጨማሪም በኦን ላይን አገልግሎት መስጠት መጀመሩንም አንስተው፤ ይህም የበለጠ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።    
'’ብቃት'’ የወጣቶች የሥራ ላይ ልምምድ በክህሎት የተቀረጹ፣ ተወዳደሪና በስራ ዓለም ብቁ የሆኑ ወጣቶችን ማፍራት ያስችላል
Jun 13, 2026 439
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ '’ብቃት'’ የወጣቶች የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም በክህሎት የተቀረጹ፣ ተወዳደሪና በስራ ዓለም ብቁ የሆኑ ወጣቶችን ማፍራት እንደሚያስችል የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰሎሞን ሶካ ገለጹ፡፡ ፕሮግራሙ ከዚህ ቀደም በ11 ከተሞች ተግባራዊ ሲደረግ የቆየ ሲሆን ዛሬ ይፋ በሆነው ፕሮግራም 16 ተጨማሪ ከተሞች የተካተቱ ሲሆን በዚህም ከ100 ሺህ በላይ ዜጎች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ለሁለት ዓመት የሚቆየው ይህ መርሐ ግብር የወጣቶችን የሥራ አጥነት ችግር በዘላቂነት ለመቅረፍና ስትራቴጂያዊ ትብብሩን ይበልጥ ለማጠናከር ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ተመልክቷል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰሎሞን ሶካ በመድረኩ እንደገለጹት፤ መንግሥት የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በተሟላ መንገድ ለማረጋገጥ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል።   በተለይ ከለውጡ ወዲህ በርካታ ዜጎች በተለያየ የሥራ መስክ ተሰማርተው ከራሳቸው አልፈው ቤተሰቦቻቸውን በማገዝ ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል፡፡ በተለይም የወጣቶችን የሥራ ዕድል አማራጭ ለማስፋት በመደበኛነት ከሚከናወኑ ተግባራት በተጨማሪ፣ ከዓለም ባንክ ጋር በመተባበር "ብቃት" የተሰኘውን የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ አንስተዋል። ይህ ፕሮግራም በከተሞች የሚኖሩ ወጣቶችን በተለያዩ ተቋማት በማሰማራት የሥራ ላይ ልምምድ እንዲያደርጉ የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰው፤ ወጣቶቹ በቆይታቸው ከሚያገኙት የተግባር ዕውቀት ባሻገር የሥራ ልምድ እንዲያገኙና በቀላሉ ወደ ሥራ እንዲገቡ የሚያግዝ መሆኑንም ተናግረዋል። ይህ የሥራ ላይ ልምምድ መርሃ ግብር በቀጣይ በሚከናወነው የማስፋፊያ ሥራ ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 29 የሆኑ፣ 12ኛ ክፍልና ከዚያ በታች የሆኑ ሴቶችንና ወጣቶችን ይበልጥ ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ገልጸዋል፡፡ ወደ ፕሮግራሙ የምትገቡ አዳዲስ ከተሞች ከነባር ከተሞች የተገኙ መልካም ተሞክሮዎችን በመቅሰም ለላቀ ውጤት መዘጋጀት አለባችሁ ሲሉም ሚኒስትር ዴኤታው አስገንዝበዋል፡፡   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አስፋው ለገሰ፤ ''ብቃት'' የተሰኘው የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም የስድስት ወር የሥራ ላይ ሥልጠና ቆይታ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ፕሮግራሙ የከተማዋ ወጣቶች በመረጡት ዘርፍ ሥልጥነው ወደ ሥራ እንዲሰማሩ ትልቅ አቅም መሆኑንም ተናግረዋል፡፡   የአማራ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አወቀ ዘመነ በበኩላቸው፤ "ብቃት" የተሰኘው የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም በክልሉ ሰባት ከተሞች ተግባራዊ እየተደረገ እንደሚገኝ አመላክተዋል፡፡ ፕሮግራሙ በክልሉ 12ኛ ክፍል እና ከዚያ በታች የትምህርት ዝግጅት ያላቸውን ወጣቶች ተጠቃሚ ለማድረግ ጉልህ ሚና እያበረከተ ይገኛል ብለዋል፡፡
በክልሉ የፈጠራ ሥራዎችን በመደገፍ ለሁለንተናዊ ልማት ያላቸውን አበርክቶ ለማሳደግ የተጀመረው ጥረት ይጠናከራል
Jun 13, 2026 354
ቡታጅራ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፈጠራ ሥራዎችን በመደገፍ ለሁለንተናዊ ልማት ያላቸውን አበርክቶ ለማሳደግ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገለጸ። በክልሉ "ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልን የሳይንስ፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ማዕከል እናድርግ" በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ የውይይት መድረክና አውደ ርዕይ በቡታጅራ ከተማ ተካሂዷል።   በመድረኩ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ሀላፊ አንተነህ ፈቃዱ እንደገለጹት፣ የሳይንስና ቴክኖሎጂ የፈጠራ ውጤቶች ለሁለንተናዊ የልማት ስራዎች ፋይዳቸው የጎላ ነው። በክልሉም ግብርናና ኢንዱስትሪን ጨምሮ በሌሎች የልማት መስኮች የሚስተዋሉ ማነቆዎችን በመፍታት በኩል ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በመሆኑም በክልሉ የፈጠራ ሥራዎችን በመደገፍ ለሁለንተናዊ ልማት የሚኖራቸውን አበርክቶ ለማሳደግ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።   በዘርፉ ተወዳዳሪ ዜጎችን ለማፍራት በትምህርት ተቋማት ላይ ይበልጥ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራም ገልጸዋል።   የክልሉ ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ቢሮ ሀላፊ ሰላሙ አማዶ በበኩላቸው እንዳሉት የሳይንስና ቴክኖሎጂ ፈጠራ ስራዎች የማህበረሰቡን ችግር በመፍታት በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ እያደረጉ ነው። የፈጠራ ባለቤቶችን በማበረታታትና ተጠቃሚነታቸውን በማሳደግ በዘርፉ እየተመዘገበ ያለውን ስኬት ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።   የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ የምርምር ሥራዎችን ለኢንዱስትሪዎች በማሸጋገር ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ ማድረግ ይገባል ያሉት ደግሞ የክልሉ ሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ ሀላፊ ሙስጠፋ ኢሳ ናቸው። በክልሉ የሚገኙ ኢንተርፕራይዞች አዳዲስ የፈጠራ ሥራዎችን ከማፍለቅ በተጨማሪ ተኪ ምርት በማምረት በኩል የሚጠበቅባቸውን ሚና እየተወጡ መሆኑን ጠቅሰዋል። ኢንተርፕራይዞቹ ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል እየፈጠሩ መሆኑን ጠቁመው፣ የዘርፉን ስኬቶች ለማጠናከር ቢሮው አበክሮ ይሰራል ብለዋል። ከዚህ ቀደም በምርምር ለከናወነው የተፈጥሮ ማዳበሪያ በሀገር አቀፍ ደረጃ እውቅና እንደተሰጠው የተናገረው ወጣት ተመስገን በቀለ፣ በክልሉ በተደረገለት ድጋፍና ክትትል በእንሰት በሽታ መከላከል የሚያስችል ምርምር ማድረጉን ተናግሯል። በመድረኩ ማጠቃለያ በቡታጅራ ከተማ በተዘጋጀ 3ኛው ዙር ክልላዊ የሳይንስና የፈጠራ ሥራዎች አውደ ርዕይ ለእይታ ከቀረቡ 146 የፈጠራ ሥራዎች ለተሻሉት እውቅናና የማበረታቻ ሽልማት ተሰጥቷል።
የኦዲት ሥራን ዲጂታላይዝ በማድረግ የኦዲት ውጤት ጥራት እንዲኖረው እየተሰራ ነው
Jun 13, 2026 310
አዳማ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የኦዲት ሥራን ዲጂታላይዝ በማድረግ ኦዲተሮች ሥራቸውን በከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲያከናውኑና የኦዲት ውጤት ጥራት እንዲኖረው እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት አስታወቀ። መሥሪያ ቤቱ ከክልሉ ለተውጣጡ ከ300 በላይ ኦዲተሮችና አመራሮች በአዲሱ የክዋኔ ኦዲት እና የፋይናንሺያል ኦዲት ማንዋል ላይ ያዘጋጀው የአምስት ቀናት የአቅም ግንባታ ሥልጠና በአዳማ ከተማ ተካሂዷል። በሥልጠናው ማጠቃለያ የተገኙት የክልሉ ምክትል ዋና ኦዲተር ቶሎሣ አቡማ በተለይ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ የኦዲት ቅልጥፍናንና ተደራሽነትን ለማስፋት ከ2019 በጀት ዓመት ጀምሮ የዲጂታላይዜሽን አሠራር ሙሉ በሙሉ ይተገበራል። ለዚህም የክልሉ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት በዓለም አቀፍ ደረጃ የኦዲተሮች ማኅበር ያወጣውን መሥፈርትና ደረጃ መሠረት ያደረገ አዲስ የክዋኔና የፋይናንሺያል ኦዲት ማንዋል ማዘጋጀቱን ጠቁመዋል። ሥልጠናውም የኦዲት አገልግሎቱን ዘመናዊ፣ ሙያዊ እና በዓለም አቀፍ መርሆች ላይ የተመሠረተ የለውጥ ጉዞ በክልሉ ለማስጀመር ትልቅ እገዛ ያደርጋል ብለዋል። የኦዲት አሠራርን ከወረቀት ንክኪ በማላቀቅ የኦዲት ሥነ-ምግባርን ለማክበርና ግልጽነትን ለመፍጠርም ትኩረት መደረጉን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት ኦዲት የሚደረጉ መሥሪያ ቤቶች ቁጥርና የመንግሥት በጀት እየጨመረ መምጣቱን ገልጸው፣ ይህንን ሊመጥን የሚችል የዲጂታላይዜሽን አሠራር መዘርጋቱን ምክትል ዋና ኦዲተሩ አስረድተዋል። ይህም ኦዲተሮች ሥራቸውን በከፍተኛ ጥንቃቄ እንዲያከናውኑና የኦዲት ውጤት ጥራት እንዲኖረው ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል ብለዋል። የክልሉ ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የፋይናንስ ኦዲት ዳይሬክተር እንዳልካቸው ታደሰ፤ ሥልጠናው በፍጥነት እየተለወጠ ካለው ዓለም አቀፋዊ የቴክኖሎጂ ሁኔታ ጋር ራስን ለማብቃት ገንቢ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። ሌላው የሥልጠናው ተሳታፊ አቶ ጢቄ አብዲሳ በበኩላቸው፣ የኦዲተር ሙያ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብትን ከብክነት መጠበቅ በመሆኑ ይህንን ኃላፊነት በብቃት ለመወጣት ሥልጠናው ዘመኑን የዋጀ መሆኑን ተናግረዋል። አቶ ገረመው አስፋ የተባሉ አስተያየት ሰጪ በበኩላቸው፣ አዲሱ ማንዋል የኦዲት ሥራን ከኋላ ቀር አሠራር ለመውጣትና የኦዲት ጥራትን ለማሻሻል ጠንካራ መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል።
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እንግልትንና አላስፈላጊ ወጪን በማስቀረት፣ ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል
Jun 13, 2026 268
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ስራ መጀመሩ እንግልትንና አላስፈላጊ ወጪን በማስቀረት ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል ሲሉ ተገልጋዮች ገለጹ። ዜጎች በመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚገጥማቸውን እንግልትና ቅሬታ ለመፍታት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት ወደ ሥራ የገባው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መንግስት ለዜጎች የሚሰጠውን አገልግሎት በማላቅ ላይ ይገኛል፡፡ አዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነቱን በማስፋት በመንግሥት አገልግሎት ጥራትን በማረጋገጥ የተገልጋዮችን እርካታ እያሳደገ ይገኛል፡፡ ኢዜአ በመዲናዋ አገልግሎት መስጠት ላይ ከሚገኙት ማዕከላት መካከል በአዲስ ከተማ እና በቂርቆስ ክፍለ ከተሞች የሚገኙ የ"አዲስ መሶብ" ቅርንጫፎችን የአገልግሎት አሰጣጥ በመቃኘት ተገልጋዮችን አነጋግሯል፡፡   በማዕከሉ ያነጋገርናቸው አካል ጉዳተኛዋ ወይዘሮ ዘነበች አለኝታ፤ ከዚህ ቀደም አገልግሎት ለማግኘት ወደ ቢሮ መመላለስ በራሱ ትልቅ ፈተና እንደነበር ገልጸዋል። ዛሬ ወደ ማዕከሉ ከገቡበት ሰዓት ጀምሮ ጉዳያቸውን ጨርሰው እስከሚወጡ ድረስ ያለው ሂደት እጅግ የተቀላጠፈ መሆኑንና በተለይም ለአካል ጉዳተኞችና ለአቅመ ደካሞች ልዩ ትኩረትና ቅድሚያ መስጠቱ ቀደም ሲል ይገጥማቸው የነበረውን እንግልት መቅረፉን ተናግረዋል።   የቂርቆስ ክፍለ ከተማ የአንድ ማዕከል ተገልጋይ ኢንስፔክተር የኔነሽ መርጋ የማዕከሉ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አሰራር ግልጽነትን በመፍጠር መጉላላትን ማስቀረቱን ገልጸዋል።   በተመሳሳይ አቶ መኳንንት ይንገስ እና ወይዘሮ ዳቤልቱ ቲቻ የሰራተኞቹ መልካም መስተንግዶና ቅልጥፍና አገልግሎቱን በፍጥነት አግኝተው ያለምንም መስተጓጎል ወደ እለት ተእለት ስራቸው እንዲመለሱ በእጅጉ እንደረዳቸው ጠቁመዋል።   የአገልግሎቱን አሰጣጥ በተመለከተ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ የሲቪል ምዝገባና የነዋሪዎች አገልግሎት ሰጪ ባለሙያ የሆኑት ይስሀቅ ተስፋዬ፤ ተገልጋዮች የተለያዩ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ ማግኘት መቻላቸው እንግልት ማስቀረቱን ተናግረዋል፡፡   የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የአንድ ማዕከል ባለሙያዋ አቢጊያ ቁምላቸው፤ በማዕከሉ ያሉ አገልግሎቶች በሙሉ ዲጂታላይዝድ መደረጋቸውን ገልጻ ይህም ቀደም ሲል በወረቀት አሰራር ወቅት የነበረውን የፋይል መጥፋትና መዘግየት ችግር ሙሉ በሙሉ በመፍታት፣ አስተማማኝና ደህንነቱ የተጠበቀ አሰራር መዘርጋቱን አብራርታለች።   የአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቴድሮስ ማስረሻ፤ ተቋማቸው ፈጣንና ቀልጣፋ አሰራርን በማስፈን የህዝቡን እርካታ ይበልጥ ለማሳደግ በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ከፍተኛ የህዝብ ፍላጎት ባለባቸው የአገልግሎት ዘርፎች ላይ ትኩረት በማድረግ፣ የአገልግሎት ጥራትንና ተደራሽነትን በየጊዜው እያሻሻሉ እንደሚገኙ አብራርተዋል።
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን የሐሰተኛ መረጃ እና የጥላቻ ንግግር ለመከላከል የሚያስችል የቴክኖሎጂ አቅሙን እያሳደገ ነው
Jun 13, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን የሐሰተኛ መረጃዎችና የጥላቻ ንግግሮችን ለመከላከል የሚያስችል የቴክኖሎጂ አቅም እያሳደገ መሆኑን ዋና ዳይሬክተሯ ሃይማኖት ዘለቀ ገለጹ። ትውልዱ በጤናማ አስተሳሰብ ለአገር ዕድገት፣ ልማትና ብልፅግና የራሱን አዎንታዊ አስተዋጽኦ እንዲያደርግ ማስቻል እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃይማኖት ዘለቀ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት ስማርት ፎን የያዘ እያንዳንዱ ዜጋ የሚሳተፍበት ሰፊ የተግባቦት ዘዴ ተፈጥሯል። ይህ አዝማሚያ ጥሩ ተሞክሮዎችን ለመለዋወጥና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ትልቅ ዕድል ይዞ የመጣ መሆኑን አመልክተው፤ በሌላ በኩል ግን ሙያዊ ሥነ-ምግባር የሌላቸው በርካታ አካላት የሚሳተፉበት በመሆኑ ትልቅ ፈተና እየደቀነ እንደሚገኝ አብራርተዋል። አብዛኛው የዲጂታል ሚዲያ ተጠቃሚ የጋዜጠኝነት ሙያዊ ሥልጠና የሌለው በመሆኑ እንደ ትክክለኛነት፣ ሚዛናዊነት እና ታማኝነት ያሉ መሠረታዊ የጋዜጠኝነት ምሰሶዎች አደጋ ላይ መውደቃቸውን ተናግረዋል። ይህም ኃላፊነት የማይወስዱ፣ ስህተታቸውን ሳያርሙ የሚያሰራጩ የይዘት ፈጣሪዎች መበራከታቸውን ጠቅሰው፤ የሐሰተኛ መረጃዎችና የጥላቻ ንግግሮች ስርጭት እንዲሰፋ ምክንያት መሆኑን አስገንዝበዋል። ትውልዱ በጤናማ አስተሳሰብ ለአገር ዕድገት፣ ልማትና ብልፅግና የራሱን አዎንታዊ አስተዋጽኦ እንዲያደርግ ማስቻል እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። የሐሰተኛ መረጃ ስርጭት አገር አጥፊ መሆኑን የጠቀሱት ዋና ዳይሬክተሯ፤ ይህንን የሚጸየፍ ትውልድ ለመፍጠር ሁሉም በጋራና በኃላፊነት ስሜት ሊረባረብ እንደሚገባ ተናግረዋል። ባለሥልጣኑ እነዚህን ተግዳሮቶች ለመከላከል አሠራሩን ከማኑዋል ወደ ዲጂታል እየቀየረ መሆኑን ገልጸው፤ ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ተቋሙን የማዘመን ሥራዎች በስፋት እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም መሠረት የተመዘገቡትንም ሆነ ያልተመዘገቡትን የዲጂታል ሚዲያ ይዘቶች በቴክኖሎጂ ለመከታተል የሚያስችል አሠራር ተዘርግቷል ብለዋል። በተለይም የሰዎችን ድምፅና ምስል በመቀየርና በማስመሰል ሕዝብን ወደተሳሳተ ውሳኔ የሚመሩ የ"ዲፕ ፌክ" (Deepfake) ቴክኖሎጂዎችን ለመቆጣጠር የሚያስችለውን የመጀመሪያ ምዕራፍ ሥራ አጠናቆ ተቋሙ ወደ ሁለተኛው ምዕራፍ መሸጋገሩን ይፋ አድርገዋል። በአሁኑ ወቅት ባለሥልጣኑ ፈቃድ የሰጣቸውን 73 የበይነ-መረብ ሚዲያዎችን የቅርብ ክትትልና ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ወደፊትም ሁሉም የዲጂታል ሚዲያ አካላት ተመዝግበውና ኃላፊነት ወስደው እንዲሠሩ የሚያስገድድ የሕግ ማዕቀፍና የአዋጅ ማሻሻያ ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን አስታውቀዋል። ከዚህ ቀደም የሐሰተኛ መረጃና የጥላቻ ንግግር ጥቆማዎች በ9192 ነጻ የስልክ መስመር ብቻ ይሰበሰቡ እንደነበር ያስታወሱት ዋና ዳይሬክተሯ፤ አሁን ግን "ኤማ አፕ" (Ema App) የተሰኘ አዲስ አፕሊኬሽን በይፋ ሥራ መጀመሩን ተናግረዋል። ይህ አሠራር በተዘረጋ በጥቂት ቀናት ውስጥ ብቻ ከ47 በላይ ጥቆማዎች በዚሁ መተግበሪያ በኩል መድረሳቸውን ጠቅሰው፤ ሊንክና ስክሪንሹት መኖሩ የመረጃውን ባለቤት በቀላሉ ለማወቅና ተጠያቂነትን ለማስፈን ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። የሐሰተኛ መረጃንና የጥላቻ ንግግርን የመከላከል ሥራ የባለሥልጣኑ ብቻ እንዳልሆነና ወደፊትም ከሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም፣ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እና ከሌሎች የዴሞክራሲያዊ ተቋማት ጋር ያለውን ትብብር ይበልጥ በማጠናከር እንደሚሠራ አስገንዝበዋል።
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር በአዳዲስ ከተሞች የሚተገበረውን የ'’ብቃት'’ የወጣቶች የሥራ ልምምድ እና የሥራ ማዕከላት አገልግሎት ይፋ አደረገ
Jun 13, 2026 111
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከዓለም ባንክ ጋር በመተባበር በአዳዲስ ከተሞች የሚተገበር የ'’ብቃት'’ የወጣቶች የሥራ ልምምድ እና የሥራ ማዕከላት አገልግሎት ይፋ አድርጓል፡፡ ፕሮግራሙ ከዚህ ቀደም በ11 ከተሞች ተግባራዊ ሲደረግ የቆየ ሲሆን ዛሬ ይፋ በሆነው ፕሮግራም 16 ተጨማሪ ከተሞች የተካተቱ ሲሆን በዚህም 100ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተጠቁሟል፡፡ ለሁለት ዓመት የሚቆየው ይህ መርሐ ግብር የወጣቶችን የሥራ አጥነት ችግር በዘላቂነት ለመቅረፍ እና ስትራቴጂያዊ ትብብሩን ይበልጥ ለማጠናከር ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ተመልክቷል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሰሎሞን ሶካ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ መንግሥት የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በተሟላ መንገድ ለማረጋገጥ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል።   በተለይ ከለውጡ ወዲህ በርካታ ዜጎች በተለያየ የሥራ መስክ ተሰማርተው ከራሳቸው አልፈው ቤተሰቦቻቸውን በማገዝ ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል፡፡ በተለይም የወጣቶችን የሥራ ዕድል አማራጭ ለማስፋት በመደበኛነት ከሚከናወኑ ተግባራት በተጨማሪ፣ ከዓለም ባንክ ጋር በመተባበር "ብቃት" የተሰኘውን የሥራ ላይ ልምምድ ፕሮግራም ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ አንስተዋል። ፕሮግራሙ በከተሞች የሚኖሩ ወጣቶችን በተለያዩ ተቋማት በማሰማራት የሥራ ላይ ልምምድ እንዲያደርጉ የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰው፤ ወጣቶቹ በቆይታቸው ከሚያገኙት የተግባር ዕውቀት ባሻገር የሥራ ልምድ እንዲያገኙ በማስቻል በቀላሉ ወደ ሥራ እንዲገቡ የሚያግዝ መሆኑን ተናግረዋል። ይህ የሥራ ላይ ልምምድ መርሃ-ግብር በቀጣይ በሚከናወነው የማስፋፊያ ሥራ ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 29 የሆኑ ሴቶችንና ወጣቶችን ይበልጥ ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ጠቅሰዋል፡፡
የዲጅታል ግብርና መስፋፋት ምርታማነትን ለማሳደግና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
Jun 12, 2026 492
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 5 / 2018 (ኢዜአ)፦የዲጅታል ግብርና አሰራር በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተስፋፋ መሆኑ ምርታማነትን ለማሳደግና የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ ዲጅታል ግብርና ከልማዳዊ የእርሻ አሰራር ወደ እውቀትና ቴክኖሎጂ መር ኢንዱስትሪ በመቀየር፣ ሀገራዊ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥና የግብርና ምርቶችን የውጭ ኤክስፖርት አቅም ማሳደግ የሚያስችል መፍትሄ ነው። በተጨማሪም ዲጅታል ግብርና ማለት ምርታማነትን ለመጨመርና ፈጣን ውሳኔዎችን ለማሳለፍ እንደ ኢንተርኔት፣ ድሮን እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ያሉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በግብርናው ዘርፍ ውስጥ መጠቀም ነው። የግብርና ሚኒስቴር ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ዓመታዊ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴንሽንና የምክር አገልግሎት ፎረም አካሂዷል።   የግብርና ሚኒስትር ዴዔታ አማካሪ ፕሮፌሰር አሊ መሐመድ በዚሁ ጊዜ፤ የዘርፉ ክፍለ ኢኮኖሚ ለሥራ ዕድል፣ ለምግብ ሉዓላዊነትና እና ለውጭ ምንዛሬ ግኝት የላቀ ሚና ያለው የአገር ውስጥ የጀርባ አጥንት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይሁን እንጂ ዘርፉ ለዘመናት በዘመናዊ አሰራር ባለመደገፉ ምክንያት፣ አገሪቱ ካላት እምቅ ሀብት አንጻር የሚገባትን ጥቅም ሳታገኝ መቆየቷ ተናግረዋል፡፡ ይህንን ችግር ለመፍታት መንግስት ዲጅታል የግብርና ስርዓትን ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩን ጠቅሰው ስርዓቱ በተለይ በአርሶ አደሩና በባለሙያው መካከል የነበረውን የመረጃ ልውውጥ ክፍተት በመሙላት ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ጠቅሰዋል፡፡ አርሶ አደሮች ሬዲዮና የእጅ ስልክን በመጠቀም ስለ አየር ንብረትና ግብዓቶች መረጃ በማግኘት በመረጃ ላይ የተመሰረተ ምርታማነትን ማሳደግ መቻላቸውን ጠቅሰዋል፡፡ አርሶ አደሩን ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግና ዘርፉን ለማላቅ የዲጅታል ግብርና ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡   በግብርና ሚኒስቴር የእርሻና ሆርቲካልቸር ኤክስቴንሽን መሪ ስራ አስፈጻሚ የኔነሽ ኤጉ በበኩላቸው፤ ድጅታል ግብርና የአርሶ አደሩን የቴክኖሎጅ አጠቃቀም ማሳደጉን ገልጸዋል፡፡ ቀደም ሲል የነበረው ኋላ ቀር የግብርና አሰራር ስርዓት ወደ ዘመናዊ በማሸጋገር ምርትና ምርታማነት በከፍተኛ መጠን እንዲጨምር ማስቻሉንም ጠቅሰዋል፡፡      
በክልሉ የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ የሳይንስና የፈጠራ ሥራዎችን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 12, 2026 311
ቡታጅራ፤ ሰኔ 5/2018 (ኢዜአ፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ችግር ፈቺ የሳይንስና የፈጠራ ሥራዎችን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፈቃዱ ገለጹ፡፡ "የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልን የሳይንስ፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ማዕከል እናድርግ" በሚል መሪ ሀሳብ በቡታጅራ ከተማ 3ኛው ዙር ክልላዊ የሳይንስና የፈጠራ ሥራዎች አውደ ርዕይ ተከፍቷል።   የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ትምህርት ቢሮ ሀላፊ አቶ አንተነህ ፈቃዱ በዚህ ወቅት እንዳሉት በክልሉ የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ የሳይንስና የፈጠራ ሥራዎችን ለማሳደግ ትኩረት ተጥቷል፡፡ በክልሉ የሚካሄደው የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂና የፈጠራ አውደ ርዕይም በዘርፉ ተሰጥኦ ያላቸው የፈጠራ ባለቤቶችን በማበረታታት ከክልሉ አልፎ በሀገር አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።   የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት የመደመር መንግስት እሳቤ ለሳይንስ፣ ለቴክኖሎጂና ለፈጠራ ሥራዎች መስፋፋት መሰረት ጥሏል። በዚህም የዘርፉን አቅም ወደ ሀብት መቀየር የሚችሉ የፖሊሲና የህግ ማሻሻያዎች ሲደረጉ መቆየታቸውን ተናግረዋል። በሳይንስ፣ በቴክኖሎጂና በፈጠራ ሥራዎች ሁሉንም ዜጋ ተሳታፊና ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል የመሰረተ ልማት ዝርጋታ መከናወኑንም ጠቁመዋል።   ለሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ትግበራው ስኬታማነት ጥራቱን የጠበቀ የትምህርት ስርዓት ወሳኝ መሆኑን ያነሱት ደግሞ በትምህርት ሚኒስቴር የአጠቃላይ ትምህርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አየለች እሸቴ ናቸው። ለዚህም አዲሱ የትምህርትና ስልጠና ፖሊሲ ለሳይንስ፣ ለምርምር፣ ለእውቀት ሽግግር፣ ለቴክኖሎጂና ለኢንዱስትሪ ትስስር፣ ለኢንተፕራይዞች ልማት መስፋፋትና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ዘርፍ ልዩ ትኩረት መስጠቱን ጠቁመዋል። የመማር ማስተማር ስራውን ከተለመደው አሰራር በማውጣት በዲጅታል ቴክኖሎጂ የታገዘ ማድረግም የዚሁ አስቻይ ሁኔታ አካል መሆኑንም ገልጸዋል። በአውደ ርዕዩ የአፈር ለምነትን በማሳደግ ምርትና ምርታማነት መጨመር የሚያስችል የተፈጥሮ ማዳበሪያ የምርምር ውጤት ይዘው መቅረባቸውን የተናገሩት ደግሞ መምህር ታምራት ተስፋዬ ናቸው። የአውደ ርዕዩ መዘጋጀት የምርምር ስራቸውን እንዲያስተዋውቁና ወደ ገበያ በማውጣት ለውጤታማነታቸው ተጨማሪ አቅም እንደሚሆናቸው ተናግረዋል።   ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ክልል አቀፍ የሳይንስ፣ ኢኖቬሽንና የፈጠራ ሥራዎች አውደ ርዕይ የፈጠራ ሥራዎችን ከማስተዋወቅ ባለፈ ለተሻሉት እውቅናና ሽልማት እንደሚሰጥ ታውቋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የፌዴራል፣ የክልሉና የምስራቅ ጉራጌ ዞን ከፍተኛ አመራሮች፣ የፈጠራ ባለቤቶችና ተማሪዎች ተሳትፈዋል።  
በስሉጥ ከተማ ስሉጥ አገልግሎት- አዲስ መሶብ
Jun 12, 2026 426
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 5 / 2018 (ኢዜአ)፦ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በአዲስ አበባ ከተማ ከታየው አስደማሚ የከተሜነት ትራንስፎርሜሽን ጎን ለጎን የሕብረተሰብ ተጠቃሚነትን ማዕከል ያደረጉ ዘመን ተሻጋሪ ሰው ተኮር ስራዎች ተሰርቷል፤ እየተሰሩም ይገኛሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ የህዝቡ የዘመናት ጥያቄ የነበረውን የአገልግሎት አሰጣጥ ጉድለት ስር-ነቀል የሆነ ለውጥ ለማምጣትም መጠነ ሰፊ የሆነ የመሰረተ-ልማት እና የሰው ኃይል ልማት እየተሰራ ይገኛል፡፡ ዕድገቷን እና ስሉጥ ከተማነቷን (Smart-city) የሚመጥን አገልግሎት ለማቅረብ ቴክኖሎጂን ተግባር ላይ የማዋል ሂደት አጠናክራ ይዛለች፡፡ ይኸውም የመሶብ አንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት ቀዳሚው ተጠቃሽ ነው፡፡   አዲስ መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት፣ በከተማዋ ሁሉም ክፍለ ከተሞች ተደራሽ በማድረግ የሕብረተሰቡን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማዘመን ቀን ከሌሊት እየተሰራ ይገኛል፤ የላቀ ውጤትም ተመዝግቦበታል፡፡ እስካሁን በማዕከል እና በዘጠኝ ክፍለ-ከተሞች እንዲሁም በተንቀሳቃሽ አውቶቡስ የተደራጀ፣ ጥብቅ ክትትልና ድጋፍ የሚደረግባቸው፣ የበቁ የሰው ኃይል የተሟላላቸው ማዕከሎች አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ በቴክኖሎጂ በታገዘ በተደረገ ዳሰሳ እንደሚያሳየው ተገልጋዩ ከ99 በመቶ በላይ እርካታ ያመላክታል፡፡ ቀሪ ሁለት ክፍለ ከተሞችም ግንባታቸው ተጠናቅቆ በጥቂት ቀናት አገልግሎት ይጀምራሉ፡፡   የአገልግሎት አሰጣጥ ጉድለትን ታሪክ ለማድረግ በቁርጠኝነት ተተግብሮ፣ የሕብተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማላቅ እንደሚሰራ የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ጽ/ቤት መረጃ ያመለክታል።
በክልሉ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በአገልግሎት አሰጣጥና በወጣቶች የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ ውጤት አምጥቷል
Jun 12, 2026 293
ሀዋሳ፤ ሰኔ 5/2018 (ኢዜአ):-በሲዳማ ክልል የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በአገልግሎት አሰጣጥና በወጣቶች የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ ውጤት ማምጣቱን የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ ገለፀ፡፡ የሲዳማ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ተፈራ በራሳ ለኢዜአ እንደተናገሩት የአምስት ሚሊዮን ኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ኢኒሼቲቭ በክልሉ በመንግስታዊ አገልግሎትና በኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ላይ ውጤት አምጥቷል። በክልሉ ሰልጥነው ምስክር ወረቀት ካገኙት ውስጥ የመንግስት ሠራተኞች፣ በተለያዩ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ ያሉ ወጣቶች እንዲሁም ተማሪዎች እንደሚገኙበት ገልጸዋል። በክልሉ ብዙ የመንግስት ሠራተኞች የዲጂታል ክህሎት ባለቤት መሆናቸው ውጤታማ መንግስታዊ አገልግሎት ለመስጠት ጉልህ ሚና መጫወቱን ተናግረዋል። ሥልጠናውን የወሰዱ ወጣቶችም በአሁን ወቅት በዲጂታል ኢኮኖሚ የሚፈጠሩ የሥራ ዕድሎችን በመጠቀም ገቢ የማግኘት ዕድላቸውን ማስፋታቸውንም አክለዋል።   በክልሉ ሥልጠናውን ወስደው ካጠናቀቁ ዜጎች መካከል በሲዳማ ክልል ጤና ቢሮ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ባለሙያ ወይዘሮ ሙሉወርቅ መኳንት አንዷ ናቸው። በተለያዩ ኮርሶች የሚሰጡ የኮደርስ ስልጠናዎችን በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት እንደወሰዱ ገልጸው በሥልጠናው የቴክኖሎጂ እውቀታቸው ያሳደጉና ለስራቸው አጋዥ የሆኑ ብዙ ክህሎቶችን ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ዲጂታል አሰራር በተለይ ለጤናው ዘርፍ አገልግሎት ቅልጥፍናና ተደራሽነት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረው፣ ስልጠናው በስራቸው አገልግሎቶችን በተሻለ መንገድ ለመስጠት አስችሎኛል ብለዋል።   ወጣት አብርሀም ጥላሁን በበኩሉ በሀዋሳ ከተማ በግል ድርጅት ውስጥ በመተግበሪያ አልሚነት ተቀጥሮ እየሰራ መሆኑን ገልጾ፣ የኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና ሁሉንም ኮርሶች መውሰዱን ተናግሯል፡፡ ድርጅቱ የተለያዩ መተግበሪያዎችን አልምቶ ለተጠቃሚዎች የማቅረብ እንዲሁም የኔትወርክ ዝርጋታ እና የኦንላይን ገበያ ላይ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልጿል። በተቋሙ የሚለሙ መተግበሪያዎች ከሰው ሰራሽ አስተውሎት ጋር አብረው እንዲሄዱ ለማድረግ ብሎም ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነታችን እንዲጨምር የኮደርስ ሥልጠና መውሰዴ ጠቅሞኛል ብሏል፡፡
የጂንካ ከተማ ዲጂታላይዝድ ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ተገልጋዮች በአጭር ጊዜ ውስጥ ጉዳያቸውን እንዲፈጽሙ አስችሏል
Jun 12, 2026 182
ጂንካ፤ ሰኔ 5 /2018 (ኢዜአ)፦የጂንካ ከተማ ዲጂታላይዝድ ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ተገልጋዮች በአጭር ጊዜ ውስጥ ጉዳያቸውን እንዲፈጽሙ ማስቻሉ ተገለጸ፡፡ የከተማው የአንድ ማዕከል ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት በከተማዋ ቀደም ሲል በአሰራር ሲስተዋል የነበረውን ችግር በመፍታት የተገልጋዮችን እንግልት ማስቀረቱን ባለጉዳዮች ተናግረዋል። የአገልግሎት አሰጣጡን አስመልክቶ ኢዜአ ካነጋገራቸው ተገልጋዮች መካከል አቶ ስሜነህ ካሳሁን እንደገለፁት፤ የማዘጋጃ ቤቱ የቀደመ አሰራር ኋላ ቀር በመሆኑ ተገልጋዩን ለውጣ ውረድ ሲያጋልጥ ቆይቷል። ይህን ችግር ለመፍታት በአሁኑ ወቅት የተጀመረው የአንድ ማዕከል ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት በዲጂታል ታግዞ መሰጠቱ በአጭር ጊዜ ውስጥ ጉዳያቸውን ለመፈጸም እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። ሌላኛው የማዘጋጃ ቤቱ ተገልጋይ አቶ አሊ ሙሐመድ በበኩላቸው፤ በአንድ ማዕከል ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት የታዩ የአሰራር ለውጦችን ወደ ሌሎች ተቋማት ማስፋት እንደሚገባ ተናግረዋል። አገልግሎቱ ከቢሮክራሲና ሙስና የፀዳ መሆኑ ቀደም ሲል በአገልግሎት አሰጣጥ ይስተዋል የነበረን የመልካም አስተዳደር ችግር መፍታቱንም አመልክተዋል። የጂንካ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤት የአንድ ማዕከል አስተባባሪ አቶ ተመስገን ጋናቡል በበኩላቸው፤ የማዘጋጃ ቤቱን አሰራር ለማዘመን ለሰው ሀይል ልማትና ለቴክኖሎጂ ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል። ማዘጋጃ ቤቱ ቀደም ሲል በወረቀት አገልግሎቶችን ሲሰጥ በነበረባቸው ወቅቶች ፋይል ከመጥፋት ባለፈ በተገቢው ባለመደራጀት ለፍለጋ ሲወስድ የነበረን ረጅም ጊዜ ለማስቀረት ወደ ዲጂታል የምዝገባ ስርአት መግባቱን ጠቁመዋል። በዲጂታል ቴክኖሎጂው የአንድ ተገልጋይ ጉዳይ ምን ያህል ጊዜ እንደፈጀ መተግበሪያው መረጃ መስጠቱ የተጠያቂነት አሰራርን በመዘርጋት ብልሹ አሰራርን ለማስወገድ ማስቻሉን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በማዘጋጃ ቤቱ ዲጂታል አገልግሎት የስም ዝውውር ለማድረግ፣ የይዞታ ማረጋገጫ ሰርተፍኬት ለማግኘት፣ የግንባታ ፈቃድ ለመውሰድ፣ ለዋስትና አገልግሎቶች እና ለማንኛውም ከመሬት ጋር ተያይዞ ለሚቀርቡ ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ እየተሰጠ ነው ብለዋል። በቀጣይም እንደ ባንክ፣ ፖስታ ቤት፣ ቴሌኮም፣ ኤሌክትሪክና እና ውሃ ያሉ አገልግሎቶችን ከማዕከሉ ጋር በማስተሳሰር ተገልጋዮች በአንድ ማዕከል ዘርፈ-ብዙ አገልግሎት የሚያገኙበት ሁኔታም እንደሚመቻች አስተባባሪው አስታውቀዋል።
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ብልሹ አሰራሮችን በማስቀረት ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጠ ነው
Jun 12, 2026 277
አሶሳ፤ ሰኔ 5 /2018 (ኢዜአ)፦ የአሶሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀደም ሲል የነበሩ የአሰራር ግድፈቶችን በማስቀረት፣ ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ተገልጋዮች ገለጹ። የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመቅረፍ እና ሁሉንም አገልግሎቶች በአንድ ጣራ ስር ተደራሽ ለማድረግ የአሶሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የአስተዳደሩን አራት ተቋማትና ከፌዴራል ሶስት ተቋማትን ይዞ ባለፈው መጋቢት ወር በ38 አገልግሎቶች ስራ መጀመሩ ይታወሳል። ይህ አዲስ አሰራር ደንበኞች ያለምንም እንግልትና ተጨማሪ ወጪ ፈጣን ምላሽ እንዲያገኙ በር የከፈተ ሲሆን፣ የአሁኑ የተገልጋዮች ምስክርነትም ተቋሙ ያስመዘገበውን ውጤታማነት በተጨባጭ የሚያሳይ ነው። በአሶሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የንብረት ውክልና ለመስጠት የመጣው ሰኢድ ጁሃር እና የንግድ ፈቃድ ለማውጣት የመጣችው ወጣት ጁፒተር አወል፤ በማዕከሉ ሁሉንም አገልግሎት በአንድ ቦታ አግኝተናል ብለዋል። አገልግሎቱ ፈጣን፣ ግልጽ እና ወጪ ቆጣቢ ከመሆኑም በላይ የተገልጋዮችን ክብር በጠበቀ መልኩ እንዲስተናገዱ በሚያደርግ የህዝቡን የመልካም አስተዳደር እጦት ጥያቄ የመለሰ ማዕከል መሆኑን ገልጸዋል። ማዕከሉ በቀጣይ ሌሎች የከተማ አስተዳደሩን ተቋማት እንዲያካትትም ተገልጋዮቹ ጠይቀዋል። በማዕከሉ ያገኘናቸው ተገልጋይ አቶ አብዱ ካሳው በበኩላቸው፤ አገልግሎቱ የጊዜ ቀጠሮን እና መጉላላትን በማስቀረት ለተገልጋዮች እፎይታን የፈጠረ እንደሆነ ገልጸዋል። የአሶሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ቢራራ ካሳ፤ ማዕከሉ ስራ ከጀመረ በጥቂት ወራት ጊዜ ውስጥ ከ1 ሺህ 600 በላይ ዜጎች የተለያዩ አገልግሎቶችን ማግኘታቸውን ተናግረዋል።   ማዕከሉ በቀን ከ 135 በላይ ተገልጋዮችን እያስተናገደ መሆኑን ገልጸው፥ በተለይም የንግድ ፍቃድ ውክልና እና ሌሎች ተያያዥነት ያላቸው አገልግሎት ፈላጊዎች በብዛት እንደሚስተናገዱ ጠቅሰዋል። በቀጣይም በከተማዋ የመልካም አስተዳደር ችግር የሚታይባቸውን ተቋማት በመለየት አገልግሎታቸውን ወደ ማዕከሉ እንዲያስገቡ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል።
መንግስት ጠንካራ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ሥርዓት ገንብቷል
Jun 12, 2026 219
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት ለሀገሪቱ ሁለንተናዊ ዕድገት አቅም የሚፈጥሩ ሙያተኞችና ቴክኖሎጂዎች ውጤታማ የሚሆኑበት ጠንካራ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ሥርዓትና ምቹ ምኅዳር መገንባቱን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢፌዲሪ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት ለተከታታይ ሶስት ቀናት የሚቆይ የመጀመሪያውን ዓለምአቀፍ የምርምር ጉባኤ እና የቴክኖሎጂ ውድድር ማካሄድ ጀምሯል። በመድረኩ የኢፌዲሪ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር (ዶ/ር)፣ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ሀገራት የመጡ ተመራማሪዎች፣ የቴክኖሎጂ ተወዳዳሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።   በመክፈቻው የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር)፤ መንግስት ጠንካራ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ሥርዓትን በመገንባት፣ ለሀገሪቱ ሁለንተናዊ ዕድገት አቅም የሚፈጥሩ ሙያተኞችና ቴክኖሎጂዎች ውጤታማ የሚሆኑበት ምቹ ምኅዳር ፈጥሯል ብለዋል። ከሀገራዊ የልማት እድገት ጋር የተናበበ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና እንዲጎለብት መንግስት የዘርፉን እድገት የሚያረጋግጡ ፖሊሲዎችና አሰራሮች ተግባራዊ ማድረጉን ጠቁመዋል። በዘርፉ ብቁ ሙያተኛን በማፍራትና ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለኢንዱስትሪላይዜሽን እድገት ምላሽ የሚሰጥ፣ አካታችና ጥራት ያለው የቴክኒክና ሙያ ሥርዓት መገንባት የሚያስችል ምኅዳር እየተፈጠረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተለይም ብቁ፣ ቴክኖሎጂ የሚያፈልቁና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ መሆን የሚችሉ ሰልጣኞችን በማፍራት በኩል አበረታች ለውጥ መመዝገቡን አክለዋል። ለእነዚህ ስኬቶች ዋና ምክንያት ከሆኑት መካከል ገበያ መር ሥልጠና፣ የኢንዱስትሪ ተሳትፎ፣ አካታችነት፣ ዲጂታላይዜሽን እንዲሁም የፈጠራ እና የኢንተርፕረነርሺፕ ሥነ-ምህዳር ማጎልበት በመቻሉ መሆኑን አስረድተዋል። በቀጣይም የኢንዱስትሪላይዜሽን እድገትን ለማፋጠንና ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ እድገት ለማስመዝገብ ጠንካራ የቴክኒክና ሙያ ሥርዓትን ማጠናከርና ከዓለም አቀፍ ሀገራት ጋር በጋራ መስራት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰዋል። ለዚህ ደግሞ የቴክኖሎጂ ምርምር ሥራዎች ወሳኝ በመሆናቸው፣ ዛሬ የተጀመረው ዓለም አቀፍ ጉባኤና የቴክኖሎጂ ውድድር የእውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲጎለብት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል።   የኢፌዲሪ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በተዘጋጀው የሦስት ቀናት ጉባኤ ዘርፉ ላይ ያተኮሩ የምርምር ጽሑፎች እንደሚቀርቡና የተመረጡ የቴክኖሎጂ ሥራዎች ለውድድር እንደሚበቁ አብራርተዋል። በዚህ ታላቅ ሁነት ላይ ከ16 በላይ ሀገራት የተውጣጡ ተመራማሪዎችና ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ መሆናቸውን አስታውቀዋል።
በክልሉ የትራንስፖርት አገልግሎት አሰጣጡን ምቹ ለማድረግ የዲጂታል አገልግሎት ዝርጋታ ላይ በትኩረት እየተሰራ ነው
Jun 12, 2026 261
አዳማ፤ ሰኔ 5 /2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የትራንስፖርት አገልግሎት አሰጣጡን ምቹና ተደራሽ ለማድረግ የዲጂታል አገልግሎት ዝርጋታ ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ትራንስፖርት ኤጀንሲ ገለጸ። በኤጀንሲው የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ሙስባሁዲን አብዱልመጅድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የትራንስፖርት አገልግሎት አሰጣጡን ምቹና ተደራሽ ለማድረግ የዲጂታል አገልግሎት ዝርጋታ ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ ነው። በዚህም መሠረት በበጀት ዓመቱ የታሪፍ ተመን፣ የሚሸፈኑ መስመሮች ርቀት እንዲሁም የትራንስፖርት መነሻና መዳረሻዎች በግልጽ እንዲታወቁ ተደርጓል ብለዋል። አሽከርካሪዎችና ረዳቶችም ይህንን አሠራር እንዲከተሉ ከማድረግ ባለፈ ተሽከርካሪዎች በተፈቀደላቸው የሥምሪት መስመር ብቻ እንዲሠሩ፣ ቦሎና የሦስተኛ ወገን መድን መለጠፋቸውን የማረጋገጥ፣ እንዲሁም የቴክኒክ ብቃትና የሥምሪት ፈቃድ ቁጥጥር ሥርዓቶች መጠናከራቸውን ገልጸዋል። ከዚህም ባለፈ ተመሳሳይ ርቀት ያላቸው ጉዞዎች ተመሳሳይ የታሪፍ ክፍያ እንዲኖራቸውና ተሽከርካሪዎች ወርሃዊ ሥምሪታቸውን በአግባቡ እንዲፈጽሙ የዲጂታል ሥምሪት አሠራር መዘርጋቱንም ተናግረዋል። በተለይም የሕዝብ ትራንስፖርት አቅርቦትና ፍላጎትን ለማጣጣም እንዲሁም አገልግሎቱን ለማዘመን የተቀናጀ የዘመናዊ መናኸሪያዎች ልማት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በጅማ፣ ነቀምቴ፣ ወሊሶ፣ ሮቤና ሻሸመኔን ጨምሮ በ17 የክልሉ ከተሞች ደረጃቸውን የጠበቁ ዘመናዊ መናኸሪያዎች ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን አስረድተዋል። መናኸሪያዎቹ ከብልሹ አሠራር የጸዳ አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ በሲሲቲቪ (CCTV) ካሜራ የተደገፈ ቀጥታ ቁጥጥርና ክትትል ከኤጀንሲው ዋና ማዕከል እየተደረገባቸው ይገኛል ብለዋል። በተጨማሪም በቡሌ ሆራና በአሰላ ከተሞችን ጨምሮ የአራት አዳዲስ ዘመናዊ መናኸሪያዎች ግንባታ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በአጠቃላይ በክልሉ በሚገኙ ሁሉም ዞኖችና 23 ዋና ዋና ከተሞች ውስጥ በሚገኙ ከ380 በላይ የሕዝብ ትራንስፖርት መናኸሪያዎች ላይ ዲጂታል የቁጥጥር ሥርዓት ተዘርግቷል ብለዋል። ቅጣት ያለባቸው አሽከርካሪዎች ካሉበት ቦታ ሆነው በተንቀሳቃሽ ስልካቸው ክፍያ መፈጸም የሚችሉበት ሥርዓት መዘርጋቱንም አክለዋል። ኤጀንሲው በቀጣዩ በጀት ዓመት አገልግሎቱን ይበልጥ ለማዘመንና ተደራሽ ለማድረግ አቅዶ እየሠራ መሆኑን የገለጹት አቶ ሙስባሁዲን፤ ተገልጋዮች በቴሌብር አማካኝነት ካሉበት ሆነው የሚፈልጉትን ተሽከርካሪ የጉዞ ትኬት መቁረጥ የሚችሉበትን አሠራር ተግባራዊ ለማድረግ እየተሠራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
በሌሎች ዘርፎች የተመዘገቡትን ስኬቶች በቴክኖሎጂውም...
Jun 12, 2026 2266
በዮሐንስ ደርበው ኢትዮጵያ ለፈታኝ ሁኔታዎች የማይበገር ኢኮኖሚን ለመገንባት በምታደርገው ጥረት በርካታ ስኬቶችን አስመዝግባለች። በአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ፣ በአረንጓዴ አሻራ ፣ በስንዴ ልማት ፣ በቱሪዝምና በሌሎችም ዘርፎች የተመዘገቡት ስኬቶች ለዚህ ተጠቃሽ ናቸው። አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን ጨምሮ በቴክኖሎጂ መስክም ተወዳዳሪ ሀገርና ወጣት ለመፍጠር ዘርፉ ላይ ኢንቨስት አስፈላጊ እንደመሆኑ በትኩረት እየተሰራበት ነው። ካለፈውም፤ ከዛሬውም በላቀ ከፍታ ቴክኖሎጂን ነገ የመጠቀም ሁኔታ ስለሚሰፋ በዚህ ዐውድ ንቁ ተዋናይ የመሆንን አዋጭነት በመገንዘብ እንደሌሎቹ ኢንሼቲቮች ለዲጂታሉ ዘርፍ የተሰጠው ትኩረትም በዘርፉ ኢትዮጵያን የሚያስጠራ ነው። ለአብነትም፤ ሐምሌ 16 ቀን 2016 ዓ.ም. ጅማሮውን ያደረገው ‎የ5 ሚሊየን የኢትዮጵያ ኮደሮች አሁንም በነጻ በስፋት እየተሰጠ ነው። ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በኮምፒውተር ፕሮግራሚንግ፣ በመረጃ ትንተና፣ በአንድሮይድ ሶፍትዌር ልማት እና በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ ትምህርቶች 5 ሚሊየን 5 ሺህ 146 ሠልጣኞች ተመዝግበዋል። ከ3 ሚሊየን የሚልቁት ደግሞ ሥልጠናውን አጠናቅቀዋል። ከዚህ አኳያ የኢትዮጵያ ወጣቶች ሁሌም በመጠየቅ፣ በመማር፣ አዳዲስ ነገሮችን በመፈለግ ያላቋረጠ ጥረት እየተጉ ለተለዋዋጩ ቴክኖሎጂ ዝግጁ መሆን ይገባቸዋል። በላቀ የአየር ትራንስፖርት፣ በኮሪደር ልማት፣ በቱሪዝም፣ በግብርና እንዲሁም በሌሎች መስኮች በምሳሌነት እንደተነሳችው በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስም ሆኔ በቴክኖሎጂው ዘርፍ ከፍ ያለ ደረጃ መድረስ ትችላለች። ኢትዮጵያን የሚመጥን ከተማ የመገንባት ሂደት እንግልትንና ብልሹ አሠራርን መቅረፊያ ብልኀት የብርቱዎቹ ልጆች ብርታት በቀጣይ ቶሎ ምልክት የማያሳየው፤ ምልክቶቹ ከታዩ በኋላም ወዲያው ካልታከመ ለአዕምሮ ዕድገት ውስንነት የሚዳርገው በሽታ ባሳለፍነው ጥር ወር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) በተገኙበት 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 10ኛ መደበኛ ስብሰባ ሲካሄድ፤ በሪፎርም ሥራችን ቴክኖሎጂ ላይ ኢንቨስት እያደረግን ያለነው በዘርፉ ተወዳዳሪ ሀገርና ወጣት ለመፍጠር ነው ማለታቸው ይታወሳል። ከአምሥቱ ብዝኃ ዘርፎች አንደኛው ቴክኖሎጂ የሆነበት ምክንያት ነገ ለትውልድ ካለው ፋይዳ አንጻር መሆኑንም አጉልተዋል። ለዚህም አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን በማሳያነት ጠቅሰው፤ የዛሬ ሥድስት ዓመት ገደማ ኢትዮጵያ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ስታቋቁም አንድም የአፍሪካ ሀገር በተቋም ደረጃ ኤ አይ አለመፍጠሩን በማንሳትምኢትዮጵያ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲ እየገነባች መሆኗን እና ቢበዛ እስከ አንድ ዓመት ባለው ጊዜ ሥራ እንደሚጀምርም መጠቆማቸው ይታወሳል። ይህ ሁሉ ዝግጅት የሚደረገው አባቶቻችን የኢትዮጵያ አየር መንገድን በጊዜው መሥርተው ዛሬ ከአፍሪካ አንደኛ እንደሆነው፤ የኢትዮጵያ አየር ኃይልንም በጊዜው መሥርተው ዛሬ በአፍሪካ ቀዳሚ አየር ኃይል ከሚባሉት አንዱ እንደሆነው ሁሉ፤ ነገም የእኛ የኤ አይ ዩኒቨርሲቲ እና ተቋም በአፍሪካ ውስጥ ስመጥር መሆን እንዲችል፣ የተስተካከለ መሠረት ይዞ እንዲነሳ በሪፎርም ውስጥ አንደኛ ቁልፍ ጉዳይ አድርገን ስንሠራ ቆይተናል ሲሉ አረጋግጠዋል። ለተሻለ ነገ እየተደረጉ ካሉ በርካታ ዝግጅቶች አንዱ፤ በግል ቢሆን ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቀውን የ5 ሚሊየን ኮደሮች ሥልጠና መንግሥት በነጻ ማቅረቡ ይገኝበታል። ይህ ኢኒሼቲቭ ከተያዘለት ጊዜ ቀድሞ ስኬታማ በመሆኑ፤ ውድ ኢትዮጵያውያን ለ5 ሚሊየን ኮደሮች ምዕራፍ ስኬት እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)። በሦስት ዓመታት ውስጥ ለማሳካት የታቀደውን ግብ ከሁለት ዓመት ባነሰ ጊዜ ውስጥ ማሳካት ተችሏልም ብለዋል። ይህ ስኬት የሕዝባችንን ቁርጠኝነት እና ወሰን የሌለው ዐቅም ማረጋገጫ ነው ሲሉም ገልጸዋል። ‎ከዛሬ 10 ዓመት ገደማ ጀምሮ ዓለም ለሥራ ከሚፈልጋቸው ሰዎች መካከል ከሞላ ጎደል 50 በመቶው የሚገኘው አፍሪካ ውስጥ እንደሚሆን በማመላከት፤ ይህንን ዕንቁ ዕድል በወጉ ተረድቶ ወጣቱን ለነገ ውድድር ማዘጋጀት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ከዚህ አንጻር የኢትዮጵያ ሪፎርም ምን ያህል ትውልድ ላይ አበክሮ እንደሠራ ለማየት አንዱ መገለጫ ቴክኖሎጂ መሆኑን እንገነዘባለን። ስለዚህ ‎በዲጂታሉ ዓለም በልኩ ለመዘጋጀት የጀመርነው ታሪካዊ ምዕራፍ የጉዟችን ማብቂያ ሳይሆን ብሔራዊ ርዕያችንን ይበልጥ የምናፋጥንበት መነሻ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ እስከ ነሐሴ 2018 ዓ.ም. ድረስ የሠልጣኞችን ቁጥር 7 ሚሊየን ለማድረስ የተሰነቀውን ግብ ለማሳካት እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ የዚህ ብሔራዊ ተልዕኮ አካል እንዲሆን ጥሪ አቅርበዋል። ለተማሪዎች ባስተላለፉት መልዕክትም በመጭው የክረምት ወቅት ጊዜያችሁን በዋዛ ከማሳለፍ ተቆጥባችሁ፤ በመመዝገብና በመማር ወደ ትምህርት ገበታችሁ ስትመለሱ ተማሪዎች ብቻ ሳትሆኑ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያላችሁ የዲጂታል መሪዎች እንድትሆኑ አሳስባለሁም ብለዋል። በሌላ በኩል ባሳለፍነው ታኅሣሥ ወር ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓልን በማስመልከት በተዘጋጀ የውይይት መድረክ ላይ ከምሁራን ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሲሰጡ፤ ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያ ትልቅ ተስፋ ያላት ሀገር መሆኗን ተናግረዋል። ከተማርን፣ ዝግጁ ከሆንን፣ እየሠራናቸው ያሉትንና በቀጣይ የምናከናውናቸውን ጨምሮ በመተባበር ለለውጥ ዝግጁ ሆነን በትጋት ከሠራን፤ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሂደት የማይናቅ ደረጃ ላይ እንደርሳለን ብለዋል። በተመሳሳይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በታኅሣሥ ወር በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ተደራሽ፣ ፍትሐዊ እና አስተማማኝ የዲጂታል ምኅዳር መፍጠር ላይ ማተኮሩን አስታውቀዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስኬታማ እንደነበር አውስተው፤ ለማሳያነት ያህል በሕዝብ መገልገያ ዲጂታል መሠረተ-ልማቶች ዝርጋታ ውጤታማ ሥራ መከናወኑን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ወሳኝ በሚባል ደረጃ ከጥሬ ገንዘብ ግብይት ወደ ዲጂታል የፋይናንስ ሥርዓት መሸጋገሯንም እንዲሁ። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030፤ ተደራሽነትን ማስፋት፤ እኩል ዕድል ማመቻቸትና በተቋማትና ሕዝብ መካከል መተማመንን መፍጠር የተሰኙ ሦስት ቁልፍ ትልሞችን ሠንቆ በትግበራ ላይ ይገኛል። አሁን ላይ በኢትዮጵያ ጠንካራ የሳይበር ደኅንነት ተቋም መገንባቱንም አረጋግጠዋል በወቅቱ። ይህም ለዲጂታል 2030 ስኬታማነት የራሱን ሚና ያበረክታል ነው ያሉት። የትውልዱ የዲጂታል አጠቃቀም ከኢትዮጵያ ባሕል፣ ዕሴትና ሉዓላዊነት ጋር በተናበበ መልኩ ሊሆን እንደሚገባም መክረዋል። ቴክኖሎጂን ጨምሮ በተለያዩ በርካታ መስኮች ምቹ ምኅዳር ለመፍጠር በመሪነት ስኬታማ ተግባራት እያስመዘገቡ ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) ባሳለፍነው ሚያዝያ ወር በአፍሪካ ሕብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ ሆነው መሾማቸው ይታወቃል። ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራር እና ሀገራቸው በአኅጉሩ የሰው ሠራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ለምትገኘው የላቀ ሚና ዕውቅና የሰጠም ነው። ይህም ልክ እንደሌሎች መስኮች በቴክኖሎጂው ዘርፍም በትክክለኛው መንገድ እየተጓዘች መሆኗን ይመሠክራል። አሁን ላይ ኢትዮጵያ፤ ከእርሻ እስከ ፍርድ ቤት፣ ከመንገዶች እስከ የመንግሥት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ድረስ፤ ቀልጣፋ፣ ተደራሽ እና ዜጎችን ማዕከል ያደረጉ አገልግሎቶችን የሚሰጥ የዲጂታል ሥነ-ምኅዳር እየገነባች ነው። ለዚህ ደግሞ የሚሠራው ሁሉ ለበለጸገች ኢትዮጵያ ነውና መንግሥትን ማገዝ፣ ኃላፊነትን በአግባቡ መወጣት፣ ለሀገር የሚበጀውን በተነሳሽነት ለመፈጸም በይበልጥ ቁርጠኛ መሆን ያስፈልጋል። ሀገር በቴክኖሎጂ ስትልቅ የሕዝቡ የኑሮ ዘይቤ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ አገልግሎት አሰጣጥና ተያያዥ ሰው ተኮር ጉዳዮች ቀላል፣ ፈጣን እና ምቹ እንደሚሆኑም መገንዘብ ይገባል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂና ፋይዳዎች እንደሚያመላክቱት እንደ ሀገር በዘርፉ አበረታች ውጤቶች እየተገኙ ነው። በቀጣይ በቴክኖሎጂው መስክ ከዓለም ጋር እኩል ለመሄድ እንዲቻል፤ በነጻ እየተሰጠ ያለውን የ5 ሚሊየን ኮደሮች ሥልጠና አጠናክሮ በመቀጠል ዜጎች ልንጠቀምበት ይገባል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ‎የምትገነቡት ነገ የሚጀምረው ዛሬ ነው።
የአንድ ማዕከል አገልግሎቱ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና ፍትሀዊ አገልግሎት መስጠት ያስችላል
Jun 11, 2026 374
ነቀምቴ፤ ሰኔ 4/2018(ኢዜአ)፦ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የመንግስት አሰራርን ዲጂታላይዝድ በማድረግ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና ፍትሀዊ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል በኦሮሚያ ክልል የነቀምቴ ከተማዋ ከንቲባ አቶ መሰረት ሀይሉ ገለጹ። የነቀምቴ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።   በመርሃ ግብሩ የከተማዋ ከንቲባ አቶ መሰረት ሀይሉ እንደገለጹት፣ ማዕከሉ የመንግስት ተቋማት አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝድ በማድረግ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ነው። የአገልግሎቱ ዲጂታላይዝድ መሆን ብልሹ አሰራሮችን በማስቀረት የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ከመፍታት ባለፈ የተገልጋዩን ጊዜና ጉልበት እንደሚቆጥብም ተናግረዋል። የተለያዩ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ ማስተናገድ የሚችለው ማዕከል ወደ ሥራ መግባት ማህበረሰቡ ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ሲያነሳ የነበረውን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ይፈታል ብለዋል።   ማዕከሉ የተቋማትን አሰራር በማዘመን በ12 መስኮት 128 አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ መስጠት እንደሚያስችልም ገልጸዋል። ለማዕከሉ ግንባታ ከ400 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ መደረጉን ገልጸው፣ ከ200 ሺህ በላይ የከተማዋን ነዋሪዎች እንደሚያገለግል ጠቁመዋል። በከተማዋ የተገነባው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የተቋማትን አሰራር በማዘመን ብልሹ አሰራርን ለማስቀረት የራሱ ድርሻ እንዳለው በማዕከሉ አገልግሎት የሚሰጡ ባለሙያዎች ተናግረዋል።   ከአስተያየት ሰጪዎቹ ባለሙያዎች መካከል ተሰማ ሙለታ እንዳሉት መንግስት በአገልግሎት አሰጣጥ ህብረተሰቡ ሲያነሳው የነበረውን ቅሬታ ለመፍታት የዘረጋቸው አሰራሮች የሚበረታቱ ናቸው። ዘመናዊ አሰራሩ ከዚህ በፊት በፋይል መጥፋትና በአሰራር ችግር ይከሰት የነበረን የደንበኛ ምልልስ በመቅረፍ የተገልጋይ እርካታን እንደሚያሳድግ ገልጸዋል። ማዕከሉ ለሥራ ያለውን አመቺነት በመጠቀም የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ በትጋት እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል።   ሌላኛዋ የማዕከሉ ባለሙያ ወይዘሮ ለሊሴ ለታ ማዕከሉ ወደ ሥራ መግባቱ በመንግሥት መስሪያ ቤቶች ውስጥ የሚስተዋለውን የተገልጋይ እንግልት ለማስቀረት ይረዳል ብለዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የተለያዩ መንግስታዊ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ በማቀናጀት ለህብረተሰቡ ቀልጣፋ፣ ግልጽና ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት የሚያግዝ ነው።
የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ ስማርት አዲስ አበባን በመፍጠር እመርታዊ ውጤት እያስገኘ ነው
Jun 11, 2026 387
አዲስ አበባ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ ስማርት አዲስ አበባን በመገንባት እመርታዊ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የአዲስ አበባ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ ገለጸ። በአዲስ አበባ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ አስተባባሪነት ችግር ፈቺ አሰራሮችን በነፃ በማልማት የከተማ አስተዳደሩ ተቋማት እንዲጠቀሙ ያደረጉ የግል ተቋማትና ባለሙያዎች የእውቅና መርሃ ግብር ተካሂዷል።   የአዲስ አበባ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ ኃላፊ አዋሌ መሀመድ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ችግር ፈቺ የቴክኖሎጂ አሰራሮችን ላበለፀጉ ለአምስት ተቋማትና ዘጠኝ ባለሙያዎች እውቅና ተሰጥቷል። ስማርት ሲቲ አዲስ አበባን በመገንባት ሂደት በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሙያዊ ዕውቀትና ክህሎታቸውን ለበጎ ዓላማ በማዋል ድጋፍ ላደረጉ የግል ተቋማትና ሙያተኞች ምስጋና አቅርበዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ተግባራዊ የተደረገው የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂም በስማርት ሲቲ ትግበራ አዲስ አበባን በመገንባት እመርታዊ ውጤት እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የአዲስ አበባ ተቋማት ለተገልጋዮች ፈጣንና ቀልጣፋ የዲጂታል አገልግሎት በመስጠት ዕድገትን የሚያሳልጥ ፈጣን የለውጥ ምኅዳር መፍጠራቸውን ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ቱሉ ጥላሁን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የስማርት ሲቲ እሳቤና ግንባታ ከተማዋን ለነዋሪዎችና ጎብኚዎች ምቹ እያደረጉ ነው ብለዋል።   የስማርት ሲቲ ትግበራ ትብብርን የሚጠይቅ መሆኑን አንስተው፤ ዛሬ እውቅና ያገኙ አካላትም የተቋማትን ችግር በመፍታት የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን መመለስ የሚያስችል ተግባር ማከናወናቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም አዲስ አበባ ያላትን ፀጋ ተጠቅማ ወደ ተሻለ ደረጃ እንድትሻገር የቴክኖሎጂ ሽግግርና ሌሎች የለውጥ ስራዎች ላይ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ ሊወጣ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ዕውቅና ካገኙት መካከል የሜድኮ ቴክኖሎጂ ሶሉሽንስ ከፍተኛ ፕሮጀክት አስተዳደር አቤል ደረጄ እንዳለው፤ የከነማ ፋርማሲ አሰራርን የሚያዘምንና የተቀላጠፈ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ሲስተም አበልፅጓል።   ከጓደኛው ጋር በመሆን የመስሪያ ቦታ አሰጣጥ ስርዓቱን ሙሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል የሚቀይር ዘመናዊ የፈጠራ ሥራ አበርክተናል ያለው ደግሞ ጌታቢል መንግስቱ ነው።   ሁሉም ህብረተሰብ ባለው አቅም ሀገሩን ለማሳደግ የበኩሉን ሚና እንዲወጣም ወጣቶቹ ጥሪ አቅርበዋል።
በክልሉ ዘመናዊ የመንግስት አገልግሎትን ተደራሽ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል-ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Jun 11, 2026 304
ዲላ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዘመናዊ የመንግስት አገልግሎት ለህብረተሰቡ ተደራሽ የማድረግ ውጤታማ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። የዲላ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዛሬ በርዕሰ መስተዳድሩ አቶ ጥላሁን ከበደ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።   ማዕከሉ በክልሉ ሦስተኛው ሲሆን ብዝሃ አገልግሎቶችን በማቀፍ ለማህበረሰቡ ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ እንደሚያስችልም ተመላክቷል። ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በዚህ ወቅቱ እንዳሉት መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሰራርን ከማዘመን ባለፈ የአገልጋይነት ባህል የሚገነባና የተገልጋይ እርካታን የሚያሻሽል ነው። በተለይ ብዝሀነት ባለበት እንደ ደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የዜጎችን እንግልት በመቀነስ ረገድ ድርሻው የጎላ ነው ብለዋል። በክልሉ ዘመናዊ የመንግስት አገልግሎትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ የማድረግ ውጤታማ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል። የለውጡ መንግስት ዘመናዊ አገልግሎቶችን ተደራሽ ለማድረግ ከአንድ ማዕከል አገልግሎት እስከ ሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም የደረሰ ውጤታማ ተግባራትን ማከናወኑን ያነሱት ደግሞ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) ናቸው።   በማዕከሉ በአራት የፌደራል እና በአምስት የክልል ተቋማት የሚሰጡ 32 የተለያዩ የአገልግሎት አይነቶች ይሰጣሉ ብለዋል። ይህም በአንድ ማዕከል የዜጎችን ክብር በጠበቀ መልኩ ብዙ አገልግሎቶችን ተደራሽ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረው፣ መሰል አገልግሎቶችን የማስፋት ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በክልሉ ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው የዲላ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በወላይታ ሶዶ እና በአርባ ምንጭ ከተሞች ከተገነቡት ቀጥሎ ሦስተኛው መሆኑ ታውቋል።
የነዋሪዎችን መረጃ በዘመናዊ መንገድ የማደራጀት ሥራ ለአገልግሎት አሰጣጥ መሳለጥና ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ወሳኝ ሚና አለው
Jun 11, 2026 391
አዲስ አበባ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት መረጃዎችን በዘመናዊ መንገድ ለማደራጀት እየተከናወነ ያለው ሥራ የአገልግሎት አሰጣጥን ቀልጣፋ ከማድረግ ባለፈ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረው የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለፁ። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ ከተማ የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ የነዋሪዎችን መረጃ በዘመናዊ መንገድ ለማደራጀት እየተከናወነ ያለውን ተግባር ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።   የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ እንደሀገር የዲጂታላይዜሽን ሥራ በተግባር የሚታይበት ደረጃ ደርሷል። በተለይም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የተሰሩ ስኬታማ ሥራዎች አይተኬ ሚና መጫወታቸውን ተናግረዋል። በመሆኑም እነዚህ ስኬታማ ሥራዎች ይበልጥ ለማጠናከር መረጃን የሚያሰባስቡ ማናቸውም የሕዝብ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት አሰራራቸውን ሙሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል ማሻገር አለባቸው ብለዋል። በተለይም በሲቪል ምዝገባ ረገድ ከውልደት እስከ ሞት ያሉ ማንኛቸውም የነዋሪዎችን መረጃዎችና ሰነዶች ከባህላዊ የወረቀት አያያዝ ወጥተው በዲጂታል መንገድ መያዝ እንዳለባቸው ተናግረዋል። ይህም ተቋማዊ አሰራርን በማዘመን ረገድ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ የመረጃዎች ዲጂታል መሆን ቢሮክራሲን በማስቀረት ፍጹም ግልፀኝነትን ያረጋገጠ አሰራር ለመዘርጋት እንደሚያስችል ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የያዘችውን የዲጂታል 2030 ራዕይ ስኬታማ ለማድረግ የበኩሉን ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወት አመላክተዋል። በዚህ ረገድ የአዲስ አበባ ከተማ የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ የጀመረው የሰነድ አስተዳደር ሥርዓት በሁሉም የመንግሥት ተቋማት ዘንድ ተሞክሮው ሊሰፋ የሚገባው ነው ብለዋል። ይህም ዜጎች በቀላሉ መረጃዎችን ማግኘት የሚችሉበትን የኦንላይን አገልግሎት ሥርዓት ለመዘርጋት እንደ ማሳያ የሚወሰድ ተግባር መሆኑም አስረድተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ የሲቪል ምዝገባ እና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮሴፍ ንጉሴ በበኩላቸው፤ ህዝቡ በቤቱ ሆኖ አገልግሎት ማግኘት የሚያስችለውን አዲስ የአሰራር ስርዓት ለመዘርጋት ሰፊ ስራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል ብለዋል።   ይህም ለዘመናዊ አገልግሎት አሰጣጥ መሰረት እንደሆነ ተናግረው፤ተገልጋዩ አገልግሎቱን በኦንላይን ይጠይቃል፣ እኛም በቀጥታ የምንሰጥበትን ቀልጣፋ ሂደት ይፈጥራል ብለዋል። አሰራሩ ተግባራዊ መደረጉ የአገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን እንግልትን ሙሉ በሙሉ እንደሚያስቀር ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም