ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ቀጣናዊ ዘላቂ ሰላምና እድገትን በምርምር ማገዝ አለባቸው
Apr 29, 2026 279
ጅማ፤ ሚያዝያ 21/2018(ኢዜአ)፦ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የምርምር ሥራዎቻቸውን ከቀጣናዊ ተጨባጭ ሁኔታዎች ጋር በማስተሳሰር ዘላቂ ሰላምና የጋራ እድገት ለማምጣት ያላቸውን አቅም ማጠናከር እንዳለባቸው የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ ገለፁ። "ቀጣናዊ ሰላምና ትብብር ለዘላቂ ልማት" በሚል መሪ ሀሳብ በጅማ ዩኒቨርሲቲ ዓለምአቀፍ የምርምር ጉባኤ እየተካሄደ ነው። በጉባኤው በቪዲዮ ኮንፍረንስ መልዕክት ያስተላለፉት የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ ቀጣናውን በልማት ለማስተሳሰር በሚደረግ ጥረት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማቱ በጥናትና ምርምር መደግፍ አለባቸው። ለዚህም ኢኮኖሚያዊ ትስስርን የሚያሳድጉና ማህበራዊ ፈተናዎችን ለመፍታት የሚያግዙ የፖሊሲ መነሻ ሀሳቦችን በጥናትና ምርምር እንዲያፈልቁ አስገንዝበዋል። በተለይም ሀገረሰባዊ እውቀቶችን በምርምር በማስደገፍ በቀጣናው ሀገራት በዘመናዊ አስተዳድር ሥርአት ውስጥ የሚካተቱበትን አቅም መፍጠር ላይ ይበልጥ ማተኮር አለባቸው ብለዋል። የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ጀማል አባፊጣ (ዶ/ር) በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው ከተለያዩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ለሀገርና ለቀጣናዊ ችግሮች መፍትሄ የሚሆኑ የተለያዩ የጥናትና ምርምር ሥራዎችን ማበርከቱን ጠቅሰዋል። የአየር ንብረት ለውጥ በቀጣናው እያደረሰ ያለውን ተጽዕኖ ለመከላከል ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያከናወነችው ተግባር በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው ያሉት ደግሞ በኢትዮጵያ የግሎባል ግሪን ግሮውዝ ኢንስቲትዩት (GGGI) ተወካይ ኦኬቹኩ ዳንኤል ኦግቦናያ ናቸው። የአፍሪካ ሕብረት በ2063 የሀይል፣ የውሀ ሀብትና ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን አጀንዳን ለማሳካት በሚያደርገው ጥረት የኢትዮጵያን ልምድ ሊቀስም ይገባል ሲሉም አመልክተዋል። በካናዳ የዩርክ ዩኒቨርሲቲ ተወካይ ፕሮፌሰር አሊ አስጋሪ ኢትዮጵያ ለቴክኖሎጂ አቅርቦትና ለአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ እድገት የሰጠችው ትኩረት የሚደነቅ መሆኑን ጠቅሰዋል። በምርምር ጉባኤው በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን፣ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ፣ በዲፕሎማሲ፣ በጤና፣ በትምህርትና ሌሎች ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ጥናቶች በተመራማሪዎች፣ በፖሊሲ አውጪዎችና ባለሙያዎች እየቀረቡ ነው።
በአማራ ክልል በቴክኖሎጂ የተደገፈ የኩነቶች ምዝገባ ሥርዓትን በማጠናከር የተገልጋዩን እርካታ ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
Apr 29, 2026 219
ባህር ዳር፤ ሚያዚያ 21/2018(ኢዜአ)፦ በቴክኖሎጂ የተደገፈ የኩነቶች ምዝገባ ሥርዓትን በመተግበር የተገልጋዩን እርካታ የማሳደግ ተግባሩን አጠናክሮ እንደሚቀጥል የአማራ ክልል የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አገልግሎት አስታወቀ። የክልሉ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አገልግሎት ባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ያለማውን የኩነቶች መመዝገቢያ ሲስተም ዛሬ ተረክቧል። የአገልግሎቱ ኃላፊ ወይዘሪት መዓዛ በዛብህ በርክክቡ ወቅት እንደገለጹት የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አገልግሎትን ውጤታማ ለማድረግ ዲጂታል ቴክኖሎጂ መጠቀም አስፈላጊ ነው። ለዚህም ተቋሙ በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ለምቶ ዛሬ የተረከበው የኩነት መመዝገቢያ ሲስተም መሰረታዊ ጉዳይ ነው ብለዋል። አሁን ላይ የለማው የኩነት መመዝገቢያ ሲስተም የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባን ዲጂታላይዝድ በማድረግ ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እንደሚያስችልም ተናግረዋል። ቴክኖሎጂው ስራውን ከማቀላጠፍ ባሻገር ጥራት ያለው መረጃን ለተጠቃሚው ማህብረሰብ ተደራሽ ለማድረግ እንደሚያግዘው አስረድተዋል። ይህም በክልሉ በተመረጡ 477 የምዝገባ ጣቢያዎች ሲስተሙ ቀደም ብሎ ተግባራዊ ተደርጎ ሲፈተሽ መቆየቱንም አመልክተዋል። በዚህም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ለትራንስፖርት፣ ለወረቀት፣ ለህትመትና ሌሎች ወጪዎች ይወጣ የነበረን 11 ሚሊዮን ብር ማዳን ተችሏል ብለዋል። በቀጣይም አገልግሎቱ በቴክኖሎጂ የተደገፈውን የኩነቶች ምዝገባ ስርአትን በማጠናከር የተገልጋዩን እርካታ ማሳደግ ላይ አተኩሮ እንደሚሰራ አንስተዋል። የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት መንገሻ አየነ (ዶ/ር) በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በምርምርና ሌሎች ተግባራት ተወዳዳሪነትቱን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ለዚህም የክልሉን ተቋማት ዲጂታላይዝድ ለማድረግ ከክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ጋር በመተባበር የጀመረውን ተግባር አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል። እስካሁንም ለተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎችና የመንግስት ተቋማት ሲስተም በማልማትና በመዘርጋት ሥራቸውን ለማቀላጠፍ የሚያስችል ሥራ መስራቱን ተናግረዋል። የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ ደመቀ ቦሩ በዩኒቨርሲቲው የለማው የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ሲስተም በዕቅድ ላይ የተመሰረተ ክልላዊ ልማት ለማካሄድና ፖሊሲና ስትራቴጂን ለማውጣት ያግዛል ብለዋል።
የከተማ አስተዳደሩ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን አሰራሩን በማዘመን በታላቅ የሽግግር ሂደት ላይ ይገኛል -ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 29, 2026 143
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን አሰራሩን በቴክኖሎጂ በማዘመን በታላቅ የሽግግር ሂደት ላይ እንደሚገኝ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የከተማ አስተዳደሩ ደንብ ማስከበር ባለስልጣን እያከናወነ የሚገኘውን የሪፎርም ሥራዎች ጎብኝተዋል። ከንቲባዋ በጉብኝቱ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ከተማ አስተዳደሩ ለተቋም ግንባታ የሰጠው ትኩረት ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው ብለዋል። ተቋማት ቀጣይነት ያለው ሥራ እንዲሰሩና የአገልግሎት አሰጣጣቸውም ዘላቂ እንዲሆን የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም የደንብ ማስከበር ባለስልጣን ትልቅ ማሣያ ነው ብለዋል። ተቋሙ ከቅጣት ይልቅ ለህብረተሰቡ ግንዛቤ መስጠት ላይ እየሰራ መሆኑን አብራርተው፤ የደንብ ጥሰት ተፈጽሞ ሲገኝ ብቻ ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ባለስልጣኑ በቴክኖሎጂ ራሱን በማዘመንና በመረጃ ላይ በመመስረት ሕግና ሥርዓትን ወደ ማስከበር መሸጋገሩን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ባለስልጣኑ ወረቀት አልባ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የከተማዋ የስማርት ሲቲ ግንባታ አንዱ አካል መሆኑን ገልጸዋል። አሰራሩን በሞባይል መተግበሪያም ጭምር በመስጠት ቀልጣፋ አገልግሎት ተደራሽ ማድረግ መጀመሩንም ተናግረዋል። ማህብረሰቡ የደንብ ጥሰት ሲፈጸም ካለበት ቦታ ሆኖ ጥቆማ የሚሰጥበት ዘመናዊ አሰራር መዘርጋቱንም ጠቅሰዋል። የደንብ ማስከበር ባለስልጣን አሰራሩን በማዘመን በታላቅ የሽግግር ሂደት ላይ እንደሚገኝም አረጋግጠዋል።
የመንግስት ሰራተኞች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸው በቴክኖሎጂ መስክ የመወዳደር አቅማቸውን ለማሳደግ አስችሏል
Apr 29, 2026 98
ገንዳውኃ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸው በቴክኖሎጂ መስክ አቅማቸውን በማሳደግ ተወዳዳሪነታቸው እንዲጨምር ማድረጉን በምዕራብ ጎንደር ዞን የሚገኙ የመንግስት ሰራተኞች ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በመላው ሀገሪቷ የተጀመረው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በቴክኖሎጂ የበቃና ተወዳዳሪ የሰው ሀይልን ለማፍራት አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። 5 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን ተጠቃሚ ለማድረግ ያለመው ሀገር አቀፍ ስልጠና ዲጂታል ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግም አበርክቶው የላቀ ነው። ስልጠናው ፕሮግራሚንግ፣ በዳታ ሳይንስ፣ በአንድሮይድና በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መስኮች ዜጎች ባሉበት ቦታ በበይነ-መረብ የሚከታተሉት ነው። በምዕራብ ጎንደር ዞን የመንግስት ኮሙኒኬሽን ባለሙያ የሆኑት አቶ ብሩክ ወርቄ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው በመሆኑ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ነው። ስልጠናው የቴክኖሎጂ እውቀትንና ክህሎትን በማሳደግ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ይበልጥ ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን በተግባር አረጋግጠናል ነው ያሉት። በዞኑ የመተማ ወረዳ አስተዳደር ሰራተኛ የሆኑት ወይዘሮ ሳራ ወንድሙ በበኩላቸው፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዓለም ካለበት የስልጣኔ ደረጃ እኩል ለመራመድ የሚያስችል ነው ብለዋል። "አለም በቴክኖሎጂ እየተመራች ባለችበት በዚህ ወቅት፣ እኛም እንደ አንድ የመንግስት ሰራተኛ ራሳችንን ማዘመንና ማብቃት ይጠበቅብናል" ነው ያሉት። ባገኙት ስልጠና ተጠቅመውም መረጃዎችን በዲጂታል ዘዴ በመሰብሰብ፣ በማቀናበርና ለተገልጋዩ ህብረተሰብ ቀልጣፋ ምላሽ ከመስጠት አንፃር አዲስ እይታ የፈጠረላቸው መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቡድን መሪ አቶ ስሜነው ተላከ ፤ ስልጠናው የኮምፒውተር ፕሮግራሚንግና የዳታ አያያዝ ተግባራቸውን ለማቅለል እንዳስቻላቸው አስረድተዋል። ስልጠናው የላቀ ቅልጥፍና እና ጥራት ያለው አገልግሎት ለመስጠት ከማስቻሉም በላይ አለምአቀፍ እውቅና ያለው የምስክር ወረቀት በማግኘታቸው ተወዳዳሪነታቸው ለማሳደግ አስችሎናል ብለዋል።
የኢትዮጵያን የፈጠራ ባለቤትነት መብት ጥበቃ ከዓለም አቀፍ መመዘኛዎች ጋር የሚያጣጥም የሕግ ማሻሻያ እየተደረገ ነው
Apr 29, 2026 151
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን የፈጠራ ንብረት ባለቤትነት መብት ጥበቃ ከአህጉራዊና ዓለም አቀፍ መመዘኛዎች ጋር የሚያጣጥም አዳዲስ የሕግ ማሻሻያ እየተደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ገለጸ። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል ለኢዜአ እንዳሉት፤ የአዕምሯዊ ንብረት ጥበቃ የሚሹ ሃብቶች ሕጋዊ ጥበቃ እንዲደረግላቸው ለሚጠይቁ ዜጎች አገልግሎት እየተሰጠ ነው። የአዕምሯዊ ንብረት መብትና ባለቤትነት ጥበቃን ለማዘመንም ዘመናዊ የአሰራርና የሕግ ማዕቀፎችን በማዘጋጀት ተግባራዊ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ለአብነትም ረጅም ዘመናትን ያስቆጠሩ ተቋማዊ ሕግጋትን በማሻሻል ዘመኑን የዋጀ የአሰራር ሥርዓት እንዲፈጠር መደረጉን አንስተዋል። የአሰራርና የሕግ ማዕቀፎቹም የኢትዮጵያን የአዕምሯዊ ንብረት መብትና ባለቤትነት ጥበቃ ሊደረግላቸው የሚገቡ ሃብቶችን ማስጠበቅ እያስቻሉ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የአዕምሯዊ ንብረት ባለቤትነት መብት ጥበቃ ከዓለም አቀፍ መመዘኛዎች ጋር የሚያጣጥም አዳዲስ የሕግ ማሻሻያ እየተደረገ እንደሚገኝም አስገንዝበዋል። የባለስልጣኑ ዘመናዊ የአሰራርና የሕግ ማሻሻያም የአዕምሯዊ ንብረት መብትና ባለቤትነትን በማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በተጨማሪም የሙያተኞችን የመፈጸም አቅም በማጎልበት የአገልግሎት ጥራትና ተደራሽነትን የሚያረጋግጥ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ከዓመታት በፊት በተለያዩ ዘርፎች ይሰጥ የነበረውን ከ3ሺህ የማይበልጥ የአዕምሯዊ ንብረት መብትና ባለቤትነት ጥበቃ አሁን ላይ በዓመት ወደ 9ሺህ ምዝገባ ማድረግ የሚቻልበት አቅም መፈጠሩን ጠቅሰዋል። በኢትዮ-አሊያንስ አድቮኬሲ የአዕምሯዊ ንብረትና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ደሱ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ጥበቃ የሕግ ማሻሻያዎች አሰራርን በማዘመን ገንቢ ሚና አላቸው ብለዋል። የኢትዮጵያን የአዕምሯዊ ንብረት ጥበቃ ውጤታማነትን ለማረጋገጥም የዓለም አቀፍ ተቋማትን ትብብር የበለጠ ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያን የአዕምሯዊ ንብረት ሃብቶች ጥበቃ የበለጠ ለማጠናከር ሕግጋትን ማዘመንና የሙያተኞችን ብቃት ማጎልበት እንደሚገባ ተናግረዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅና በማላመድ የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ ተችሏል
Apr 28, 2026 159
ዲላ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅና በማላመድ የግብርና ምርታማነትን ማረጋገጥ መቻሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የይርጋጨፌ ግብርና ምርምር ማዕከል ግንባታ ማስጀመሪያ የመሠረት ድንጋይ የማስቀመጥ መርሃ ግብር ተካሄዷል። ማዕከሉ ለጌዴኦ፣ ለቡርጂ፣ ለኮሬ ዞኖች የግብርና ምርምር በተለይም የቡና እና የእንሰት ምርታማነትን ለማሻሻል ትኩረት ተደርጎ እንደሚገነባም ተመላክቷል። በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት፤ በክልሉ ምርምርን መሠረተ ያደረገ የግብርና ልማትን በማረጋገጥ የአርሶ አደሩን ችግር ለማስወገድ እየተሠራ ነው። በተለይ ቴክኖሎጂን በማፍለቅ፣ በማላመድና አዳዲስ የምርምር ሙከራዎችን በማከናወን ረገድ በርካታ ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። የቡና ዝርያ ለማሻሻልና አሰራርን ለማዘመን በተደረገ ጥረት በሞዴል አርሶ አደሮች ማሳ በሄክታር እስከ 20 ኩንታል የቡና ምርት ለማምረት መቻሉን ለአብነት ጠቅሰው ይህንን ማስፋት ዋናው የማዕከሉ ተልዕኮ ነው ብለዋል። በተያዘው ዓመት ብቻ በሰብልና እንስሳት ጨምሮ በአምስት የግብርና ምርምር ዘርፎች 39 ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጉን ያነሱት ደግሞ የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አብዮት መብራቴ (ዶ/ር) ናቸው። የምርምር መሠረተ ልማትን በማስፋትና የተመራማሪዎችን ቁጥር በማሳደግ የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል ጥረት እየተደረገ መሆኑን አንስተው የይርጋጨፌ የግብርና ምርምር ማዕከልም የዚሁ አካል ነው ብለዋል። ማዕከሉ ለጌዴኦ፣ ለቡርጂና ለኮሬ ዞኖች በግብርና ምርምር በተለይም የቡና እና የእንሰት ምርታማነትን ለማሻሻል ትኩረት አድርጎ እንደሚሠራም ተናግረዋል። ይህም በክልሉ ሶስት ብቻ የነበሩትን የምርምር ማዕከላት የይርጋጨፌን እና የሳውላ ምርምር ማዕከላትን በመጨመር ወደ አምስት የሚያሳድግ ነው ብለዋል። የይርጋጨፌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ቡኔ በበኩላቸው ፤በወረዳው ከ16 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት በቡና ልማት የተሸፈነ መሆኑን ገልፀዋል። በወረዳው የቡናን ተፈጥሯዊ ጣዕም ጠብቆ ምርታማነቱን ለማሳደግ በተደረገ ጥረት በሞዴል አርሶ አደሮች ማሳ በሄክታር እየተገኘ ያለውን የከፍተኛ ምርት ተሞክሮ ለማስፋት የምርምር ማዕከሉ መገንባቱ ድርሻው የጎላ መሆኑንም አመልክተዋል። የማዕከሉን ግንባታ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት እንደሚሰሩ ያረጋገጡት ደግሞ የክልሉ ኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አረጋ በዴቻ ናቸው። ከ68 ሚሊዮን ብር በላይ የተመደበለት ማዕከሉ የመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ በሚቀጥሉት ስድስት ወራት የሚጠናቀቅ ሲሆን የአስተዳደር ህንጻ፣ ቤተሙከራ፣ የምርምር ማካሄጃ ስፍራዎችና መሰብሰቢያ አዳራሾችን ያካተተ መሆኑም ተገልጿል።
ትውልዱ በቴክኒክና ሙያ ያገኘውን ክህሎት ለእድገት በተግባር መተርጎም ይጠበቅበታል
Apr 27, 2026 197
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018(ኢዜአ)፦ ትውልዱ በቴክኒክና ሙያ መስክ የሚያገኛቸውን ክህሎቶች በተግባር በመተርጎም ለእድገት የበኩሉን ሚና ሊጫወት እንደሚገባ የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ ገለጸ። የተፈሪ መኮንን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የ100ኛ ዓመት የአልማዝ ኢዩቤልዩ በዓል የመዝጊያ ሥነ-ሥርዓት "ዘመን ተሻጋሪ ቅርስ ለቀጣዩ ትውልድ" በሚል መሪ ሃሳብ በተለያዩ መርሃ-ግብሮች ተከብሯል። በሥነ-ሥርዓቱ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች፣ የኮሌጁ መምህራንና ተማሪዎች፣ የቀድሞ ተማሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በመድረኩ በኮሌጁ የተሰሩ የቴክኖሎጂ ውጤቶች አውደ-ርዕይ፣ የኪነ-ጥበብ ስራዎችና የባህል አልባሳት ትዕይንት ቀርበዋል። የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ሃላፊ ሚደቅሳ ከበደ በዚሁ ወቅት፤ የከተማ አስተዳደሩ የገበያውን ፍላጎት መሰረት ያደረገ ብቁ ሙያተኛ ለማፍራት በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ሰልጣኞች በቂ ክህሎት እንዲጨብጡ ከኢንዱስትሪዎችና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅት ከቴክኖሎጂ ዕውቀት ውጪ ልማትና ዕድገት ማረጋገጥ እንደማይታሰብ ጠቁመው፤ በዚህ በኩል ተማሪዎች የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት በብቃት ሊወጡ ይገባል ብለዋል። የተፈሪ መኮንን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዋና ዲን ተሾመ ፈይሳ በበኩላቸው፤ ባለፉት አሥርት ዓመታት እንጦጦ በሚል ስያሜ ሲጠራ የቆየው ኮሌጅ፤ ዛሬ "ተፈሪ መኮንን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ" ተብሎ በይፋ የሚሰየምበት ዕለት በመሆኑ በዓሉን ልዩ ያደርገዋል ብለዋል። በዓሉን ከማክበር ባለፈ በቴክኒክና ሙያ መስክ የታነፀ ትውልድ ለማፍራት የተጀመረው ስራ ተጠናክሮ የሚቀጥልበት ነው ሲሉም ተናግረዋል። የቀድሞ ተፈሪ መኮንን ተማሪዎች ማኅበር ፕሬዚዳንት ደጀኔ ተዘራ እንደተናገሩት፤ ማኅበሩ ኮሌጁን ለማጠናከር በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ላይ በንቃት እየተሳተፈ ነው። የስያሜው መስተካከል ከ100ኛ ዓመት በዓሉ ጋር መገጣጠሙ ከፍተኛ ደስታ እንደፈጠረባቸው ገልጸዋል። የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማኅበር ፕሬዚዳንት ልጅ ዳንኤል ጆቴ መስፍን በበኩላቸው፤ ኮሌጁ ለሀገር ኩራት የሆኑ በርካታ ሙያተኞችን ማፍራቱን ተናግረዋል። በቀጣይም የካበተ ልምዱን ለሌሎች የሚያጋራበት ምቹ ሁኔታ ሊመቻች እንደሚገባም ጠቁመዋል። የአልማዝ ኢዩቤልዩ በዓሉ ከመጀመሪያው ጀምሮ እስከ መዝጊያው ሥነ-ሥርዓት ድረስ ስኬታማ እንዲሆን አስተዋጽኦ ላበረከቱ ባለድርሻ አካላት ምስጋና ቀርቧል።
የሰው ሰራሽ አስተውሎትን በሁሉም ተቋማት ገቢራዊ ማድረግ የሚያስችል የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት እየተገነባ ነው
Apr 27, 2026 272
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦የሰው ሰራሽ አስተውሎትን በሁሉም ተቋማት ገቢራዊ ማድረግ የሚያስችል የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት እየተገነባ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፓርክ ገለጸ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ይታወቃል። ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራርና ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ የሰው ሰራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ላለው የላቀ ሚና የተሰጠ እውቅና ነው። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት እንደገለጸው፤ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ሹመት ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን ሥነ ምግባራዊ መርሆች በተከተለ መልኩ በማልማት፣በመመራመር እንዲሁም ተግባራዊ በማድረግ በኩል ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር እንድትሆን ለተሰሩ ስራዎች እውቅና የሰጠ ነው። በኢትዮጵያ በአፍሪካ የመጀመሪያ የሆነውን የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲ ለመክፈት የሚያስችሉ ዝግጅቶችን ጨምሮ በዘርፉ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ።ለዚህ ስኬትም የተለያዩ ተቋማት በቅንጅት በርካታ ስራዎችን እያከናወኑ ይገኛሉ። በዚህም የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፓርክ ሀገርን በአፍሪካ ቀዳሚ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፓርክ ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ስኬትና ለዲጂታል ኢትዮጵያ-2030 ዕቅድ አዳዲስ የፈጠራ ዕሳቤዎችን በማፍለቅ ጉልህና ገንቢ ሚና እየተወጣ ነው። የኢትዮጵያ ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፓርክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ በለጠ እሱባለው ለኢዜአ እንዳሉት፤ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ለአመራር ልህቀትና ቴክኖሎጂ ልማት አስገዳጅ እየሆነ መጥቷል። የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ፓርኩም የሰው ሰራሽ አስተውሎት መሠረተ ልማት በማስፋፋት በኢትዮጵያ አስቻይ የዲጂታል ከባቢ ለመፍጠር እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የፋይበር፣ ፓወርና ሌሎች የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን በማሟላት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሥርዓትን የሚያዘምን ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ተናግረዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ከግብ ለማድረስም በሰው ሰራሽ አስተውሎትና በዲጂታል ክህሎት የበለጸገ የሰው ሃይል ማፍራት እየተቻለ መሆኑን አስረድተዋል። የአፍሪካ ዲጂታልና ኢኖቬሽን ቴክኖሎጂ አካዳሚ የቦርድ ሊቀ መንበርና የአፍሪካ ቴክኖሎጂ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ባህሩ ዘይኑ፤ ኢትዮጵያ በዲጂታል መሠረተ ልማት ወሳኝ ሽግግር እያደረገች ነው ብለዋል። ለአብነትም የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዓለም አቀፍ ተፅዕኖን በመገንዘብ ኢንስቲትዩት በማቋቋምና የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ የመክፈት ዝግጅት መኖሩ ትልቅ ስኬት መሆኑን ገልጸዋል። የግሉ ዘርፍም የዲጂታል ልማት አስቻይ የፖሊሲ ማዕቀፎችን በመጠቀም ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማትን የሚያሳልጥ የሰው ሰራሽ አስተውሎት መተግበሪያን ማልማት እንዳለበት አስገንዝበዋል። የአፍሪካ ዲጂታልና ኢኖቬሽን ቴክኖሎጂ አካዳሚም የኢትዮጵያን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዕውቀትና ክህሎት ለማሳደግ እገዛ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የአፍሪካ ዲጂታልና ኢኖቬሽን ቴክኖሎጂ አካዳሚ ተባባሪ መስራችና ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፕሮፌሰር ሸጋው አናጋው፤ የተቋማትን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ትግበራ ለማፋጠን የስልጠና አቅም ወሳኝ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲም በዘርፉ በዕውቀትና ክህሎት የበለጸጉ ዜጎችን በማፍራት ሁሉንም ተቋማት ብቁ የዲጂታል መሠረተ ልማት ለማስታጠቅ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። የሁሉንም ተቋማት የዳታ ሥርዓት የማሰባሰብና መተንተን አቅም ለማጎልበት የመንግስትና የግል ተቋማት ትብብርን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። በቀጣይም በኢትዮጵያ የስታርት አፕ ፖሊሲ ማዕቀፍ በዳታ ሳይንስ፣ ሰው ሰራሽ አስተውሎትና በሮቦቲክስ ዘርፍ ብቁ ወጣቶችን ለማፍራት የግሉን ዘርፍ አቅም ለማጠናከር እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።
መንግስት ለወጣት የዲጂታል ሥራ ፈጣሪዎች ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር ባለፈ አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገ ነው
Apr 25, 2026 463
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 17/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ መንግስት ለወጣት የፊንቴክ ስታርትአፖች ምቹ ሁኔታን ከመፍጠር ባለፈ አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኢንተርፕሪነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት (EDI) እና ከተባበሩት መንግሥታት ካፒታል ልማት ፈንድ (UNCDF) ጋር በመተባበር፣ ላቅ ያለ የፈጠራ ሥራ ላሳዩ ስምንት የፊንቴክ (FinTech) ስታርትአፖች የገንዘብ ሽልማት መርሀ ግብር አካሂዷል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ በሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደገለጹት፤ መንግሥት ለወጣት የዲጂታል ሥራ ፈጣሪዎች ምቹ ሁኔታን ከመፍጠር ባለፈ ተገቢውን ድጋፍ እያደረገ ይገኛል። መርሐ ግብሩ በኢትዮጵያ የዲጂታል ፋይናንስ ዘርፍን ለማዘመንና የወጣቶችን የፈጠራ አቅም ለማበረታታት ያለመ መሆኑን ጠቁመዋል። የፊንቴክ መፍትሔዎች ለግብርና፣ ለቱሪዝም፣ ለኢንዱስትሪና ለጠቅላላው የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ያላቸው ፋይዳ የላቀ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። ለዚህም በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ እንደ ቴሌ ብር እና ሲቢኢ ብር ያሉ ውጤቶች ለበርካታ ዜጎች የፋይናንስ ተደራሽነትን ማሳደጋቸውን በአብነት ጠቅሰዋል። የዘርፉን ተደራሽነት ለማስፋት ወጣቶች የሚፈጥሯቸው ዲጂታል መፍትሔዎች ለዲጂታል ሽግግር ወሳኝ ሚና እንዳላቸው አስገንዝበዋል። ከ300 በላይ የፊንቴክ ስታርትአፖች መካከል 33ቱ ተለይተው ለፉክክር መቅረባቸውን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፤ በዛሬው ዕለት ስምንት ምርጥ ስራ ፈጣሪዎች አሸናፊ በመሆን ከአጋር ድርጅቶች የተገኘውን የ20 ሚሊዮን ብር ሽልማት አግኝተዋል ብለዋል። አሸናፊዎቹ የተሰጣቸውን የገንዘብ ድጋፍ የንግድ ሞዴሎቻቸውን በተጨባጭ የገበያ ሁኔታ ለመፈተሽና ለማሳደግ እንዲጠቀሙበት ጥሪ አቅርበዋል። ከተሸላሚዎቹ መካከል የአበዳሪ መተግበሪያ ፈጣሪ ፌቨን ሽመልስ እና የኡጆ መተግበሪያ ፈጣሪ አቤኔዘር እንግዳ፣ መንግሥት ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት አድንቀዋል። ከተሸላሚዎቹ መካከል የ"አበዳሪ" መተግበሪያ ፈጣሪ ፌቨን ሽመልስ በበኩሏ፤ የብድር አቅርቦትና አሰባሰብን የሚያቀላጥፍ ቴክኖሎጂ በማበልጸግ ለዘርፉ መፍትሄ ማቅረቧን ገልጻለች። በተመሳሳይ የ"ኡጆ" መተግበሪያ ፈጣሪ አበኔዘር እንግዳ፣ ባህላዊውን የዕቁብ ሥርዓት በቴክኖሎጂ ለማዘመን ለጀመረው ሥራ መንግሥት የሰጠውን ትኩረትና ድጋፍ አድንቋል። ሽልማቱ ለጀመሩት የፈጠራ ሥራ መነሻ ካፒታል ከመሆኑ ባለፈ፤ ለሌሎች ወጣቶችም ትልቅ መነሳሳትን እንደሚፈጥር ገልጸዋል።
የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት እንግልትና አላስፈላጊ ወጪን አስቀርቶልናል - ተገልጋዮች
Apr 25, 2026 193
ሆሳዕና፤ ሚያዝያ 17/2018 (ኢዜአ)፦ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት እንግልት እና ያልተገባ ወጪን እንዳስቀረላቸው በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሆሳዕና ከተማ ተገልጋዮች ገለፁ፡፡ በማዕከሉ አገልግሎት በማግኘት ላይ የነበሩት አቶ ዮናስ ሴራሞ ለኢዜአ እንደገለፁት ፤የገቢ ግብር ጉዳይ ላይ አገልግሎት ለማግኘት ወደ ማዕከሉ እንደመጡና ባጠረ ጊዜም የሚፈልጉትን ፈጽመው ለመመለስ መቻላቸውን ነው የሚገልጹት። የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ተገልጋይን ከአላስፈላጊ ከሆነ እንግልትና ወጪ እንደሚታደግ በተግባር ያረጋገጡ መሆኑንም ተናግረዋል። የግብር ከፋይነት መለያ ቁጥር ለማውጣት ወደ ማዕከሉ የመጣው ወጣት ሞላልኝ ታምራት በወቅቱ አገልግሎቱን ማግኘቱን እና ማዕከሉ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ይታይ የነበረውን የመልካም አስተዳደር ችግር በመቅረፍ ለማሕበረሰቡ አስፈላጊ የሆነ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ነው የገለጸው። በማዕከሉ የተገልጋዩን ክብር የጠበቀ እና ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኝቷ እንዳስደሰታት የምትገልፀው ደግሞ ወጣት በረከት ዱቲሶ ናት፡፡ በፋይዳ መታወቂያዋ ላይ ያጋጠማትን የስም ስህተት በአጭር ጊዜ ማስተካከል ችያለሁ ብላለች። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ከበደ ሻሜቦ ማዕከሉ በስምንት ተቋማት 27 አገልግሎቶችን እየሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ እስካሁን ድረስ ከ 20 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አገልግሎት መስጠት መቻሉንም አስረድተዋል፡፡ በከተሞች በመሬት ዘርፍ የሚሰጡና ለብልሹ አሰራር ተጋላጭ የሆኑ አዳዲስ 48 አገልግሎቶች ተለይተዉ በማዕከሉ ውስጥ አገልግሎት ለመስጠት እንዲቻልም ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝም ገልፀዋል፡፡
ተማሪዎች ችግር ፈቺ የፈጠራ ስራዎችን እንዲያፈልቁ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል
Apr 25, 2026 183
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 17/2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ ከተማ ተማሪዎች ችግር ፈቺና ተወዳዳሪ የፈጠራ ስራዎችን እንዲያፈልቁ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር ውጤታማ ስራዎች መሰራታቸውን የከተማው ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር) ገለጹ። ቢሮው “በሳይንስና ፈጠራ የተካነ ትውልድ ለተምሳሌታዊ ሀገር” በሚል መሪ ሐሳብ ለሁለት ቀናት ሲያካሂድ የቆየው 11ኛው የሳይንስና የፈጠራ ስራ አውደ ርዕይ ተጠናቋል። በአውደ ርዕዩም በተማሪዎችና መምህራን የቀረቡ የፈጠራ ሀሳቦች ተወዳድረው የላቀ ውጤት ላመጡ ተሳታፊዎች የሽልማት አሰጣጥ ስነ-ስርዓት ተከናውኗል። የቢሮው ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ተማሪዎች ከቀለም ትምህርት ጎን ለጎን የፈጠራ ክህሎታቸውን አውጥተው እንዲጠቀሙ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል። በየዓመቱ የሚዘጋጀው ይህ የሳይንስና የፈጠራ ስራ አውደ ርዕይም ተማሪዎችና መምህራን ስራዎቻቸውን እንዲያቀርቡና የልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉ ትልቅ ዕድል የፈጠረ መሆኑን ገልፀዋል። ውድድሩ ተማሪዎችን በምርምርና በስልጠና በማገዝ ብቁና ተወዳዳሪ ትውልድ ለመቅረፅ ያለመ መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊው፤ ተማሪዎች በንድፈ ሀሳብ የተማሩትን በተግባር እንዲከውኑና ወደ ሳይንሳዊ ግኝት እንዲቀይሩ ትልቅ አቅም መፈጠሩን አስረድተዋል። በዘንድሮው አውደ ርዕይ ላይ ወደ 3 ሺህ 7 መቶ የሚጠጉ የፈጠራ ስራዎች ለውድድር መቅረባቸውን ጠቅሰው ከእነዚህም ውስጥ ከፍተኛ ውጤት ላመጡ አሸናፊዎች የእውቅና ሽልማት ተበርክቷል ብለዋል። መድረኩ ከውድድር ባለፈ ለብዙዎች የተሻለ ነገን በተስፋ ለመጠበቅ መሠረት የሚጥል መሆኑን ጠቁመው፣ ለዚህም ስኬት ከቅድመ ዝግጅት ጀምሮ በትኩረት ሲሰራ መቆየቱን ገልፀዋል። ከአውደ ርዕዩ ተሳታፊዎች መካከል የኢትዮ-ጃፓን 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ሃብታሙ ደምስ ፤ለእርሻ አገልግሎት የሚውልና በፀሐይ ሃይል የሚሰራ ትራክተር በመስራት በውድድሩ የ1ኛ ደረጃ አሸናፊ ሆኗል። ተማሪ ሃብታሙ ፤ አርሶ አደሩ ከባህላዊ የእርሻ ዘዴ ተላቆ በቴክኖሎጂ ታግዞ እንዲያመርት ለማስቻል መሣሪያውን እንደሰራ ገልጿል። በተመሳሳይ የቡርቃ ዋዮ ትምህርት ቤት ተማሪ ፌኔት በንቲ፤ በስዕልና ቅርፃቅርፅ የፈጠራ ስራ ተወዳድራ የ2ኛ ደረጃ አሸናፊ መሆን ችላለች። ተሳታፊ ተማሪዎቹ እንደገለጹት፤ መሰል አውደ ርዕዮች ያላቸውን እምቅ አቅም አውጥተው እንዲጠቀሙና ከሌሎች ተማሪዎች ልምድ እንዲቀስሙ ትልቅ እገዛ እያደረገላቸው ይገኛል።
መሶብ የአንድ ማዕከል ተንቀሳቃሽ አገልግሎት ፈጣን እና ጊዜ ቆጣቢ ነው- ተገልጋዮች
Apr 24, 2026 145
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፦መሶብ የአንድ ማዕከል ተንቀሳቃሽ አገልግሎት ወደ እኛ ከመቅረቡም ባለፈ ፈጣን እና ጊዜ ቆጣቢ ሆኖ አግኝተነዋል ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው ተገልጋዮች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአገልግሎት ቅልጥፍናንና ተደራሽነትን ለማሻሻል ከፍተኛ ፋይዳ ይኖረዋል ተብሎ የታመነበትን መሶብ የአንድ ማዕከል ተንቀሳቃሽ አገልግሎት በይፋ መርቀው ሥራ ማስጀመራቸው ይታወቃል። በምረቃው ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደገለጹት፤ ቴክኖሎጂን ለአገልግሎት ዘርፉ እንደ ዋነኛ መሣሪያ በመጠቀም ዜጎች ጊዜ ቆጣቢ አገልግሎት እንዲያገኙ ለማስቻል በቁርጠኝነት እየተሠራ ይገኛል። የመሶብ የአንድ ማዕከል የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት አጭር ጊዜ ቢሆንም፤ በአገልግሎቱ የታየው ከፍተኛ የደንበኞች እርካታ የሥራ ሞዴሉን ውጤታማነት በተግባር ማረጋገጡንም ጠቁመዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል ተንቀሳቃሽ አገልግሎት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ጀርመን አደባባይ አካባቢ ለህዝቡ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል። በዚሁ ወቅት ኢዜአ ያነጋገራቸው ተገልጋዮች አገልግሎቱ ፈጣን እና ጊዜ ቆጣቢ መሆኑን ተናግረዋል። አቶ ኢብራሂም መሐመድ የመኪና ቦሎ ለማደስ ወደ ቦታው መሄዳቸውን ጠቁመው፤ በአጭር ጊዜ ውስጥ ጉዳያቸውን ጨርሰው መመለሳቸውን ተናግረዋል። አቶ ብስራት ኮሬ እና አቶ ዘላለም አስረስም ለመንጃ ፈቃድና ለቦሎ ዕድሳት ወደ ተንቀሳቃሽ አውቶቡሱ በማቅናት፣ በአይነቱ ልዩና ቀልጣፋ መስተንግዶ ማግኘት መቻላቸውን ተናግረዋል። ያለምንም ስጋት ጊዜያቸውንም ቆጥበው በአገልግሎቱ ተጠቃሚ በመሆናቸው መደሰታቸውን ይናገራሉ። በተንቀሳቃሽ አገልግሎቱ ውስጥ የሚሰሩት የገቢዎች ባለሙያ ጫልቱ ታደሰ፣ ይህ አሰራር የተለመደውን በአንድ ቦታ ተወስኖ የመስራት አካሄድ በመቀየር ለተገልጋዩ ብቻ ሳይሆን ለአገልጋዩም ከፍተኛ የስራ ተነሳሽነትን የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል። የንግድ ምዝገባ እና ፍቃድ ባለሙያ ብርሃኑ ፈንታው በበኩላቸው፣ ወደ ተገልጋዮች ቀርበው በቴክኖሎጂ የታገዘ ፈጣን አገልግሎት በመስጠት የመጀመሪያዎቹ ባለሙያዎች በመሆናቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል። የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈጻሚ ካባ መብራቱ፤ የመሶብ ተንቀሳቃሽ አገልግሎት ቀደም ሲል በሕዝብ ዘንድ ይነሳ የነበረውን ቅሬታ ለመፍታት መንግሥት የወሰደውን ቁርጠኛ አቋም የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል። አዲሱ እሳቤ አገልግሎትን ከቢሮ በማውጣት ወደ ሕዝብ ይዞ የመጣ ድንቅ አሠራር መሆኑን አረጋግጠዋል።
የፀደቁ ደረጃዎች በዓለም አቀፍ ንግድ ተቀባይነትን መጨመር ያስችላሉ
Apr 24, 2026 127
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018(ኢዜአ)፦ በምግብ፣ በግብርና እንዲሁም በኮንስትራክሽንና ሲቪል ምህንድስና ዘርፎች የፀደቁ ደረጃዎች፣ በዓለም አቀፍ ንግድ ተቀባይነትን ከመጨመር ባለፈ የገቢ ምርቶች ጥራት ቁጥጥር ወጥ እና አስተማማኝ እንዲሆን እንደሚያስችሉ የኢትዮጵያ የደረጃዎች ኢንስቲትዩት ገለፀ። ኢንስቲትዩቱ በምግብ፣ በግብርና እንዲሁም በኮንስትራክሽንና ሲቪል ምህንድስና ዘርፎች ላይ ያተኮሩ 66 ደረጃዎችን አጽድቋል፡፡ እነዚህ ደረጃዎች የሀገሪቱን ምርቶች በዓለም አቀፍ የንግድ ሥርዓት ውስጥ ተወዳዳሪ ለማድረግና የገቢ ምርቶችን ጥራት ለመቆጣጠር ጉልህ ሚና እንደሚኖራቸው ተገልጿል። ኢንስቲትዩቱ በምግብ ጨው ላይ የሚደረግ የደብል ፎርቲፊኬሽንን እንዲሁም ግንባታዎች ከንፋስና መሬት መንቀጥቀጥ አደጋ የመከላከል አቅማቸውን የሚያሳድጉ ዘመናዊ የኮንስትራክሽን ቴክኖሎጂ ደረጃዎች በቦርድ መጽደቃቸውን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ የኢንስቲትዩቱ የሕዝብ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ ብሩክ ሀብቴ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ የደረጃዎች ቦርድ ሚያዝያ 9 ቀን 2018 ዓ.ም ባካሄደው 5ኛ መደበኛ ስብሰባው የቀረቡለትን 66 ደረጃዎች መርምሮ አጽድቋል፡፡ ካጸደቃቸው ደረጃዎች መካከል 24ቱ አዳዲስ ደረጃዎች ሲሆኑ 42ቱ የተከለሱ መሆናቸውን ጠቅሰው ከእነዚህም ውስጥ 54ቱ አስገዳጅ ደረጃዎች ሆነው መጽደቃቸው ጠቁመዋል፡፡ በምግብና ግብርና ዘርፍ የጸደቁት ደረጃዎች በተለይ በዜጎች ጤና ላይ ትኩረት ያደረጉ መሆናቸውን ጠቁመው በምግብ ጨው ላይ ፎሊክ አሲድ ተጨምሮ እንዲመረት የሚያስገድድ አዲስ ደረጃ መጽደቁንም ገልጸዋል፡፡ ይህም በእናቶችና በሕፃናት ላይ የሚስተዋሉ የጤና እክሎችን ለመቅረፍ ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ከኮንስትራክሽን ጋር በተገናኘ የጸደቁት ደረጃዎች ኢትዮጵያ አሁን ላይ የደረሰችበትን የህንጻ ግንባታ እድገትና ዓለምአቀፍ የቴክኖሎጂ ሽግግርን ያገናዘቡ ናቸውም ብለዋል። ግንባታዎች ከንፋስና ከመሬት መንቀጥቀጥ አደጋዎች የተጠበቁ እንዲሆኑ የሚያስችሉ የቴክኖሎጂ አጠቃቀሞች የተካተቱ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ የደብል ፎርቲፊኬሽንና ዘመናዊ የግንባታ ግብአቶችን በመጠቀም የግንባታዎችን የጥራት ደረጃ ማረጋገጥ የሚያስችሉ መመሪያዎች መቀመጣቸውንም ነው የጠቆሙት፡፡ ደረጃዎቹ መጽደቃቸው ለኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለምርምር፣ ለእውቀት ሽግግርና ለሸማቾች መብት መከበር ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳላቸውም ገልጸዋል። የሀገር ውስጥ ምርቶች በዓለም ገበያ ተቀባይነት እንዲኖራቸውና የገቢ ምርቶች ጥራት ወጥ በሆነ መንገድ እንዲፈተሹ የሚያስችል መሆኑንም አክለዋል፡፡ በተጨማሪም የዜጎችን ደህንነትና የአካባቢ ጥበቃን እንደሚያረጋግጥም አቶ ብሩክ ሀብቴ አስታውቀዋል፡፡ አምራቾችና አስመጪዎች የወጡትን ደረጃዎች አውቀው ምርቶቻቸውን በደረጃው መሠረት እንዲያቀርቡና ጥራታቸውን በማሻሻል ለዜጎች ደህንነትና ለሀገር ገጽታ ግንባታ የበኩላቸውን እንዲወጡ ኢንስቲትዩቱ ጥሪ አቅርቧል።
የዩኒቨርሲቲው የጥናትና ምርምር ሥራዎች የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እያሳደጉ ነው
Apr 24, 2026 142
ወልቂጤ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፦ከመማር ማስተማር ሥራው ጎን ለጎን እያካሄደ የሚገኘው የጥናትና ምርምር ስራዎች የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እያሳደጉ መሆኑን የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ። የዩኒቨርሲቲው 7ኛው ሀገር አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስ ''በቴክኖሎጂ የታገዘ ምርምር ለዘላቂ ልማት፣ ጤና እና ሁሉን አቀፍ ደህንነት'' በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ ነው። በዚህ ወቅት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ፋሪስ ደሊል (ዶ/ር) እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ሥራው ጎን ለጎን ማህበረሰብ ተኮር የሆኑ የጥናትና ምርምር ሥራዎችን በማከናወን ለውጤት እያበቃ ይገኛል። በጤና አጠባበቅ፣ በግብርና፣ በታዳሽ የኃይል ሥርአት፣ በአስተዳደር፣ በትምህርት እና በሌሎች መስኮች ላይ የተለያዩ የጥናትና ምርምር ሥራዎች ማከናወኑንም ገልጸዋል። የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል፣ የጤና አጠባበቅ ስርዓትን ለማጠናከር፣ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል እና የአካባቢ ጥበቃ ልማትን በዘላቂነት ለማስቀጠል የተከናወኑ እነዚህ የጥናት ውጤቶች የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እያሳደጉ መምጣታቸውንም ተናግረዋል። የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የምርምር እና ቴክኖሎጂ ሽግግር ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ዮሐንስ ገብሩ (ዶ/ር) በበኩላቸው የምርምር ኮንፈረንሱ ለሁለት ቀናት እንደሚቆይ ገልጸዋል። በመድረኩም በሀገር ውስጥ ካሉ 16 ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ ተመራማሪዎች ያከናወኗቸው 31 የጥናትና ምርምር ሥራዎች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል ብለዋል። የጥናትና ምርምር ሥራዎቹ በግብርና፣ በጤና፣ በምህንድስና፣ በስነ-ምህዳር፣ በአካባቢ ጥበቃና መሰል መስኮች ላይ ማተኮራቸውን ገልጸው፣ የምርምር ውጤቶቹ በመድረኩ ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል ብለዋል። ከጅማ ዩኒቨርሲቲ የመጡት ፕሮፌሰር ሱልጣን ሱሌይማን፤ ሀገር በቀል እውቀትን በመጠቀም ለሕክምና ምርምር እና ጤናን ለማሻሻል እየተሰራ ያለው ሥራ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ዩኒቨርሲቲዎች ሚናቸውን ሊያጠናክሩ ይገባል ብለዋል። የምርምር ውጤቶቹ ወደ ታች ወርደው ጥቅም ላይ እንዲውሉ በጋራ መስራት እንደሚገባም አመልክተዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፖሊሲ ጥናት እና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አክመል መሃመድ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት፤ ክልሉ በግብርና፣ በኢንዱስትሪ እና በአገልግሎት ዘርፍ የመልማት አቅም አለው። ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመሆን የሚካሄዱ የጥናትና ምርምር ሥራዎች የክልሉን እድገት ለማፋጠን እያገዙ መሆኑን አንስተዋል። ዩኒቨርሲቲዎች ባከናወኗቸው ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎች የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። ለዚህም ምሁራንና ፖሊሲ አውጪዎች በየደረጃው ካሉ የመንግስት አመራር አካላት ጋር ተቀራርበው በመስራት የምርምር ወጤቶችን በጋራ ገምግመው ጥቅም ላይ እንዲያውሉ አቅጣጫ ተቀምጧል ብለዋል። ለሁለት ቀናት በሚቆየው ሀገር ዓቀፍ የምርምር ኮንፈረንስ ላይ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተጋበዙ ምሁራንና አመራሮች በመሳተፍ ላይ ናቸው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ህብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ ሆነው መሾማቸው ኢትዮጵያ በዘርፉ ላሳየችው እመርታ ተግባራዊ ምላሽ ነው
Apr 24, 2026 276
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ህብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂው ዘርፍ ላስመዘገበቻቸው እመርታዊ ውጤቶች ተግባራዊ ምላሽ ነው ሲሉ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወ/ሮ እፀገነት መንግሥቱ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው ተሹመዋል። ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራርና ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ የሰው ሰራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ላለው የላቀ ሚና የተሰጠ እውቅና መሆኑ ተገልጿል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ሹመቱ ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን ሥነ ምግባራዊ መርሆች በተከተለ መልኩ በማልማት፣በመመራመር እንዲሁም ተግባራዊ በማድረግ በኩል ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር እንድትሆን ለተሰሩ ስራዎች እዉቅና የሰጠ ነው በሚል ገልጾታል። ይህም አህጉራዊ ትብብር የሚፈጠርበት ብሎም ለዘርፉ ተጨማሪ ሀይል እንደሚሆን ኢንስቲትዮቱ አስታውቋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግ እና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እጸገነት መንግስቱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሹመት እጅግ የሚያስደስትና ለበለጠ ስራ የሚያነሳሳ ነው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ትላንትን መርምራ፣ የዛሬን ተጨባጭ ሁኔታ ተረድታና ነገን በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) እውቀት ላይ ተመስርታ ለመተንበይ የጀመረችው ሰፊ ስራ እውቅናን በማስገኘት ላይ እንዳለ አስታውቀዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተሰጣቸው ሹመት የመንግሥት የፈጠራ ተነሳሽነት እና የቴክኖሎጂ ቁርጠኝነት ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ከተመሰረተ አጭር ጊዜ ቢሆነውም ያስመዘገበው ውጤት ግን ለዛሬው ሽልማት ያበቃ የድካም ፍሬ መሆኑን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በአፍሪካ ቀዳሚ ተጠቃሽ ሀገር እንድትሆን የሚያደርጋትን በርካታ ተግባራዊ እንቅስቃሴዎችን እያከናወነች እንደምትገኝ ተናግረዋል። ኢንስቲትዩቱ የሚፈልቁ በርካታ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ተቋማት እንደ የባህሪያቸው ወስደው ተግባር ላይ ሊያውሉት ይገባል ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዙ ስራዎችን በመጠቀም ውጤት እያሳዩ የሚገኙ ተቋማት እንዳሉ ተናግረዋል። በፍርድ ቤቶች የጉዳዮችን ፍሰት በማሳለጥና ቅልጥፍናን በማምጣት ረገድ የሰው ሰራሽ አስተውሎት እየተጫወተ ያለውን ከፍተኛ ሚና ለአብነት አንስተዋል፡፡ የሀገርን ደህንነትና ሰላምን ለማረጋገጥ ቴክኖሎጂው ሰፊ ፋይዳ እያበረከተ እንደሚገኝም ጨምረው አስታውቀዋል። ኢትዮጵያ ያገኘችው እውቅና ለበለጠ ስራ መነሳሳትን የሚፈጥር መሆኑን የተናገሩት የቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዋ፤በቀጣይም አዳዲስ የፈጠራ ስራዎችን በመጨመር ጉዞው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩቱ ምርታማነትን ለማሳደግና አገልግሎትን ለማቀላጠፍ የጀመራቸውን ውጤታማ ተግባራት ማጠናከር አለበት
Apr 23, 2026 348
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ምርታማነትን ለማሳደግና አገልግሎትን ለማቀላጠፍ የጀመራቸውን ውጤታማ ተግባራት አጠናክሮ መቀጠል አለበት። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት የተቋቋመውን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የ2018 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ተገምግሟል። ኢትዮጵያ በሰው ሠራሽ አስተውሎት ዘርፍ በግልጽ ራዕይና ቁርጠኝነት ባስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካ አርዓያ መሆኗ ዛሬ ይፋ ተደርጋል። በዚሁ መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ሕብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ዛሬ ይፋ ተደርጓል። ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራርና ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ የሰው ሠራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ላለው የላቀ ሚና የተሰጠ ዕውቅና መሆኑ ተገልጿል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት፤ ሹመቱ ኢትዮጵያ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን ሥነ-ምግባራዊ መርሆች በተከተለ መልኩ በማልማት፣ በመመራመር እንዲሁም ተግባራዊ በማድረግ በኩል ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር እንድትሆን ለተሠሩ ሥራዎች ዕውቅና የሰጠ ነው በሚል ገልጾታል። ይህም አህጉራዊ ትብብር የሚፈጠርበት ብሎም ለዘርፉ ተጨማሪ ኃይል እንደሚሆን ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል። ዛሬ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ኢንስቲትዩት የ2018 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ገምግሟል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር) ባቀረቡት ሪፖርት፤ የኢንስቲትዩቱን ችግሮች ለመፍታት፣ ብቃትንና ምርታማነትን ለማሳደግ በመረጃ ላይ የተመሰረቱ የሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) ስርዓቶችን ማበልጸግ ላይ በትኩረት እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። በተለይም የሥራ ሂደቶችን በማዘመን የተቋማትን ብቃትና ምርታማነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በትጋት እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም በውሳኔ አሰጣጥ ላይ የሚታዩ ክፍተቶችን በመድፈን ለሀገራዊ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉልህ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል። ባለፉት ዘጠኝ ወራት ችግር ፈቺ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ምርምሮችን ማከናወን፣ ማልማት እና ተደራሽ ማድረግን ጨምሮ ምርምሮችን በሳይንሳዊ መጽሔቶች ማሳተም፣ ምርምሮችን ፓተንት ማስገኘት ላይ ውጤታማ ሥራ መሠራቱን ተናግረዋል። በግብርና፣ በትምህርት፣ በፋይናንስ፣ በጂኦ ስፓሻል፣ በሮቦቲክስ እና በቋንቋ በዘጠኝ ወራቱ ለመሰብሰብ እና ለማዘጋጀት የሚያስችል መረጃ መሰብሰብ መቻሉን አስታውቀዋል። ችግር ፈቺ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ምርምሮችን ማልማት እና ተደራሽ በማድረግ ረገድ አበረታች ሥራ መሠራቱንም ጠቅሰዋል። ምርምሮቹን ዓለም አቀፍ ፓተንት የማስገኘት እና የማሳተም ሥራ በታቀደው ልክ መከናወኑንም አብራርተዋል። የዘርፉን ሥነ-ምኅዳር መገንባት የሚያስችል ደረጃውን የጠበቀ ሀገራዊ የሰው ሠራሽ አስተውሎት መሠረተ ልማት መገንባቱንም ነው ያስረዱት። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ወይዘሮ እጸገነት መንግስቱ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢንስቲትዩቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ውጤታማና ለሌሎች አርዓያ መሆን የሚችል አፈፃጸም አስመዝግቧል። ወጣቶች የሥራ ፈጣሪ እና የቴክኖሎጂ ባለቤት እንዲሆኑ በማድረግ ረገድ እያከናወነ ያለው ሥራ አበረታች መሆኑንም ጠቅሰዋል። በሮቦቲክስ ዘርፍ እየተከናወነ ያለው ሥራና የተቋማትን አገልግሎት አሰጣጥ በማሳለጥ ረገድ እየተሠሩ ያሉ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ብለዋል። በዘጠኝ ወራቱ በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርት፣ በፋይናንስ፣ በአገልግሎት እና በሌሎች ዘርፎች የታየው አፈፃፀም አበረታች ነው ሲሉም ተናግረዋል። የሀገሪቱን ምርታማነት በማሳደግና ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን ለማፋጠን እያደረገ ያለው ጥረት የሚደነቅና ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት መሆኑንም አመላክተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ማዕከል በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 463/2012 ተቋቁሞ በመስከረም 2013 ዓ.ም በይፋ ሥራውን የጀመረ ሲሆን፤ በ2014 ዓ.ም ወደ ኢንስቲትዩትነት በማደግ “አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ለሁሉም!” በሚል መሪ ሐሳብ በጤና፣ ግብርና፣ አገልግሎት፣ ፋይናንስ፣ ትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ፣ ትምህርት እንዲሁም ሌሎች በርካታ ዘርፎች ውስጥ ቴክኖሎጂውን በማልማት ላይ የሚገኝ ተቋም ነው።
ጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ባካሄደው የሪፎርም ትግበራ በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎት እየሰጠ ነው
Apr 23, 2026 129
ባሕርዳር፤ ሚያዝያ 15/2018 (ኢዜአ)፡- ተቋማቸው ባካሄደው የሪፎርም ትግበራ በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎት መስጠት መቻሉን የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ዓለምአንተ አግደው ገለጹ። የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ተካሂዷል። በዚሁ ወቅትም አቶ ዓለምአንተ እንደገለጹት፤ የፍርድ ቤቶችን አገልግሎት ዲጂታላይዝ ለማድረግ የተቀረጸው የሦስት ዓመት ስትራቴጂ አተገባበር ተስፋ ሰጭ ውጤቶችን እያሳየ መሆኑን ተናግረዋል። በመጀመሪያው ምዕራፍ የታቀዱ የመሠረተ-ልማት ዝርጋታ፣ የኔትወርክ ሥራዎች እና የስማርት ችሎቶች ግንባታ ሥራዎች በስኬት መከናወናቸውን አንስተዋል። ይህም ባለጉዳዮች ባሉበት ሆነው በኢ-ፋይሊንግ ሥርዓት ክስ መመስረት፣ ይግባኝ መጠየቅና የጉዳያቸውን ሂደት በሞባይል መተግበሪያ መከታተል የሚያስችል ዘመናዊ አሠራር ሥራ ላይ መዋሉን አስረድተዋል። በቪዲዮ ኮንፈረንስ የሚታገዙ ስማርት ችሎቶች በመዘርጋታቸውም ሕብረተሰቡ ካለበት ሆኖ ክርክሩን እንዲያካሂድ በማድረግ የባለጉዳዮችን ወጪና እንግልት መቀነስ ተችሏል ነው ያሉት። የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ዳይሬክተር መኳንንት አገኘሁ (ዶ/ር)፤ የፍርድ ቤቶችን አሠራር ዘመናዊ በማድረግ ቀልጣፋና ፍትሐዊ አገልግሎት ለመስጠት፣ የፍትሕ ተደራሽነትን ለማስፋት፣ የዳኝነት አገልግሎት ጥራትን በማሻሻል የሕዝብን እርካታ ለማረጋገጥ ያስቻሉ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በግልጽ ራዕይና ቁርጠኝነት ባስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካ አርዓያ ሆናለች
Apr 23, 2026 131
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት በግልጽ ራዕይ፣ በሥነ-ምግባራዊ መርሆች በመመስረት በማልማት፣በመመራመርና በተግባር በማዋል ባስመዘገበችው ስኬት በዘርፉ የአፍሪካ መሪ እንድትሆን ተመርጣለች። በዚሁ መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ሕብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ዛሬ ይፋ ተደርጓል። ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራርና ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ የሰው ሰራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ላለው የላቀ ሚና የተሰጠ እውቅና መሆኑ ተገልጿል። የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ሹመቱ ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን ሥነ ምግባራዊ መርሆች በተከተለ መልኩ በማልማት፣ በመመራመር እንዲሁም ተግባራዊ በማድረግ በኩል ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር እንድትሆን ለተሰሩ ስራዎች እዉቅና የሰጠ ነው በሚል ገልጾታል። ይህም አህጉራዊ ትብብር የሚፈጠርበት ብሎም ለዘርፉ ተጨማሪ ሀይል እንደሚሆን ኢንስቲትዮቱ አስታውቋል። በሌላ በኩል ኢንስቲትዩቱ ከኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ጋር በመተባበር ያዘጋጀው "የአካባቢ ብክለት ዲጂታል ሪፖርት ማድረጊያ ሥርዓት" ዛሬ በይፋ ሥራ ጀምሯል። ይህ አዲስ የለማ መተግበሪያ የአካባቢ ጥበቃና የብክለት ቁጥጥር ሥራን በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዘ የዳታ ትንተና በማከናወን ለማዘመን እንዳለመ ተጠቁሟል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ተቋሙ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ "ኤ.አይ ለሁሉም" በሚል መርህ ሀገራዊ የልማት ግቦችን የሚደግፉ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን እያመረተ ይገኛል። ይህ መተግበሪያ ህብረተሰቡ የብክለት ጥቆማዎችን በቀላሉ እንዲያደርስና በፈጣን የዳታ ትንተና አማካኝነት ተገቢው ምላሽ እንዲሰጥ የሚያስችል መሆኑንም አስረድተዋል። የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ በረከት ፍስሃጽዮን በበኩላቸው፤ መንግሥት የአሁኑንና የቀጣዩን ትውልድ ተጠቃሚነት ታሳቢ ባደረገ የኢኮኖሚ ልማት ላይ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። አሁን የለማው መተግበሪያ መንግሥት በዘርፉ የሚወስዳቸውን የፖሊሲ ማሻሻያዎችና ፈጣን ምላሾች በዳታ ላይ የተመሠረተ እንዲሆኑ ለማድረግ እንደ ትልቅ ግብዓት የሚያገለግል መሆኑን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሥርዓቱ በተለይ በከተሞች የተገነቡ የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ እና የጽዳት ሥራዎችን በዘላቂነት ለመጠበቅ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። ቴክኖሎጂው ተቋማቸው በመረጃ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ እንዲያሳልፍና የብክለት ምንጮችን በቅርበት ለመቆጣጠር እንዲቻል አቅም ይፈጥራል ሲሉ ጠቁመዋል። "ፅዱ ኢትዮጵያን" እውን ለማድረግ ህብረተሰቡ በመተግበሪያው በኩል ጥቆማዎችን በመስጠት ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል። ይህ የዲጂታል ሪፖርት ማድረጊያ ሥርዓት መተግበር ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራና በከተሞች ውበት ረገድ የጀመረቻቸውን ስኬታማ ሥራዎች በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍ፣ የተሻለ የአየር ንብረት ለመፍጠር ለሚደረገው ጉዞ ትልቅ አበርክቶ እንደሚኖረው ተገልጿል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #AIForAfrica
ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተሰጠው ኃላፊነት ኢትዮጵያ በኤአይ ዘርፍ በአፍሪካ የያዘችውን መሪነት በጉልህ ያሳየ ነው-የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት
Apr 23, 2026 610
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦የአፍሪካ ኅብረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሰው ሠራሽ አስተውሎት እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ አድርጎ መሾሙ ኢትዮጵያ በኤአይ ዘርፍ በአፍሪካ የያዘችውን መሪነት በጉልህ ያሳየ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው በአፍሪካ ኅብረት ጉባኤ በመሾማቸው የተሰማውን ደስታ ገልጿል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የተሰጠው ኃላፊነት ኢትዮጵያን በኤአይ ዘርፍ በአፍሪካ የያዘችውን መሪነት በጉልህ ያሳየ መሆኑን ጠቅሰዋል። ሹመቱ የተሰጠው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በዘርፉ ላሳዩት አመራር እና ኢትዮጵያ በአህጉሩ የሰው ሰራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች የምትገኘውን የላቀ ሚና እውቅና የሰጠ መሆኑን አመልክቷል። ባለፉት ጥቂት ዓመታት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር፣ኢትዮጵያ በዲጂታላይዜሽን እና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፎች ያስመዘገበችው እድገት ከፍተኛ አፈጻጸም አሳይታለች። የዲጂታል መሰረተ ልማትን ማስፋፋት፣ የኢ-መንግሥት አገልግሎቶችን ሥራ ላይ ማዋል፣ በፈጠራ ሥነ-ምህዳር ላይ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ፣ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ኢንስቲትዩትን ማቋቋም እንዲሁም ሀገራዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ስትራቴጂ መንደፍ ለለውጡ ጠንካራ መሰረት የጣሉ ተግባራት መሆናቸውንም አክሏል። በተጨማሪም ራሱን የቻለ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ ለማቋቋም የታቀደው ዕቅድ፤ ምርምርን፣ የክህሎት ልማትንና አህጉራዊ ትብብርን ይበልጥ እንደሚያጠናክር የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት መግለጹ ይታወሳል። #AIForAfrica #PMOEthiopia #ኢዜአ #Ethiopian_News_Agency
ኢትዮጵያ ለአካባቢ ጥበቃ ሥራ የላቀ ውጤታማነት አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን እንደ ወሳኝ ግብዓት እየተጠቀመች ትገኛለች
Apr 23, 2026 636
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ እያከናወነች ያለችውን ውጤታማ ሥራ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመደገፍ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን እንደ ወሳኝ ግብዓት እየተጠቀመች መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) ገለጹ። ኢንስቲትዩቱ ከኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ጋር በመተባበር ያዘጋጀው "የአካባቢ ብክለት ዲጂታል ሪፖርት ማድረጊያ ሥርዓት" በይፋ ስራ አስጀምሯል። ይህ አዲስ የዲጂታል ቴክኖሎጂ የአካባቢ ጥበቃና የብክለት ቁጥጥር ሥራን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የታገዘ የዳታ ትንተና በማከናወን ለማዘመን ያለመ ነው። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ተቋሙ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ "ኤ.አይ ለሁሉም" በሚል መርህ ሀገራዊ የልማት ግቦችን የሚደግፉ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን እያመረተ ይገኛል። ይህ ዛሬ ይፋ የሆነው መተግበሪያም ህብረተሰቡ የብክለት ጥቆማዎችን በቀላሉ እንዲያደርስና በፈጣን የዳታ ትንተና አማካኝነት ተገቢው ምላሽ እንዲሰጥ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ በረከት ፍስሃጽዮን ፤ መንግሥት የአሁኑንና የቀጣዩን ትውልድ ተጠቃሚነት ታሳቢ ባደረገ የኢኮኖሚ ልማት ላይ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ዛሬ ይፋ የሆነው ዲጂታል መተግበሪያ መንግሥት በዘርፉ የሚወስዳቸውን የፖሊሲ ማሻሻያዎችና ፈጣን ምላሾች በዳታ ላይ የተመሠረተ እንዲሆን ለማድረግ እንደ ግብዓት የሚያገለግል መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ መተግበሪያው በተለይ በከተሞች የተገነቡ የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ እና የጽዳት ሥራዎችን በዘላቂነት ለመጠበቅ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። ቴክኖሎጂው ተቋማቸው በመረጃ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ እንዲወስንና የብክለት ምንጮችን በቅርበት መቆጣጠር የሚያስችል አቅም እንደሚፈጥርም ተናግረዋል። በመሆኑም ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ ህብረተሰቡ በንቃት በመሳተፍ ጥቆማዎችን በመተግበሪያው በኩል እንዲሰጥ ጥሪ አቅርበዋል። ይህ የዲጂታል ሪፖርት ማድረጊያ መተግበርያ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራና በከተሞች ውበት ላይ የጀመረቻቸውን ስኬታማ ሥራዎች በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍ የተሻለ የአየር ንብረት ለመፍጠር ለሚደረገው ጉዞ ትልቅ አበርክቶ እንደሚኖረው ተገልጿል።