ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዲጅታሉ ዓለም ተወዳዳሪና ስራ ፈጣሪ ዜጎችን ለማፍራት አስችሏል
Jul 29, 2026 25
ሆሳዕና ፤ ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ) ፡- የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ተወዳዳሪና ስራ ፈጣሪ ዜጎች ለማፍራት እያስቻለ መሆኑን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ቢሮ ገለፀ። የቢሮ ኃላፊው አቶ ሰላሙ አማዶ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በክልሉ በዲጅታል ቴክኖሎጂ ተወዳዳሪና ስራ ፈጣሪ ዜጎችን በማፍራት ረገድ ተጨባጭ ዉጤት እየተመዘገበበት ነው። በጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ234 ሺህ የሚጠጉ ዜጎች ስልጠናውን የተከታተሉ መሆኑን ነው ያመለከቱት። ስልጠናውን ከወሰዱት ዜጎች መካከል 185 ሺህ 8 መቶ በላይ የሚሆኑት የእውቅና ሰርተፍኬት አግኝተው የኦን ላይን ስራዎች ላይ በመሳተፍ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንዳገኙም ገልፀዋል። ቢሮው በዲጅታል ቴክኖሎጂው በቂ እውቀት ፣ ክህሎትና እውቅና ያገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ አማራጮችን ተግባራዊ በማድረግ ላይ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በዋቸሞ ዩኒቨርስቲ የኮምፒውተር ሳይንስ መምህርት ፀጋነሽ ሞገስ በበኩላቸው ኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዘርፉ የበረኝን እውቅት በማሻሻል በአለማቀፍ ደረጃ ተወዳደሪ ለመሆን አስችሎኛል ነው ያሉት። ስልጠናውን አጠናቀው ባገኙት የእዉቅና ሰርተፍኬት ተጨማሪ ገቢ የሚያስገኝላቸው ስራን ለመስራት እንደቻሉ ነው የተናገሩት። በሆሳዕና ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የኮምፒውተር ሳይንስ መምህርት ተስፋ በቀለ በበኩሏ፤ የኢንፎርሜሽንና ቴክኖሎጂ እዉቀትንና ክህሎትን ማሳደጋቸው ዓለም አቀፋዊ ተወዳዳሪነትን ጨምሮልኛል ነው የሚሉት። የአትዮ ኮደርስ ስልጠናም በዘርፉ የነበረኝን እውቀት እንዳሻሽልና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ በመሆን ተጠቃሚነቴን ለማሳደግ አስችሎኛል ነው ያሉት።
በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ ግልጽ የአሠራር ሥርዓት መዘርጋት የሚያስችሉ ዲጂታል መተግበሪያዎች ገቢራዊ ተደርገዋል
Jul 28, 2026 378
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 21/2018 (ኢዜአ)፦በነዳጅና ኢነርጂ ዘርፍ በዲጅታል ቴክኖሎጂ የታገዘ ግልጽ የአሰራር ሥርዓት መዘርጋት የሚያስችሉ ዲጂታል መተግበሪያዎች ገቢራዊ መደረጋቸው የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን የነዳጅ ግብይቱን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ሥርዓት መቆጣጠር የሚያስችሉ መተግበሪያዎችን አስመርቋል፡፡ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ተቋማትን በሰው ኃይልና በቴክኖሎጂ በማደራጀት ምቹ የሥራ ከባቢና ቀልጣፋ አሠራር መዘርጋት ይገባል፡፡ ዘመኑን የዋጀ በቴክኖሎጂ የተደገፈ የአሠራር ሥርዓት ለተቋማዊ ግንባታ የጎላ ሚና እንዳለው በመግለጽ፤ የዲጂታል አሠራር ቀጣይነት ይኖረዋል ብለዋል፡፡ የነዳጅና ኢነርጂ ዘርፉን አሠራር ይበልጥ ማዘመንና ግልጽነትን ማስፈን አስፈላጊ መሆኑን ያነሱት ሚኒስትሩ፤ ተመርቀው ሥራ ላይ የሚውሉት የዲጂታል ቴክኖሎጂዎች የላቀና ቀልጣፋ አገልግሎት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ገቢራዊ የተደረጉት የዲጂታል መተግበሪያዎች የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካል መሆናቸውን ገልጸው፤ ተቋማዊ አሠራርን በቴክኖሎጂ ማዘመን ቀጣይነት ይኖረዋል ብለዋል፡፡ የነዳጅ ዘርፉን ብልሹ አሠራር በሕጋዊ የአሠራር ሥርዓት ከመቆጣጠር ባሻገር በዲጂታል ቴክኖሎጂ መደገፍ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የተቀናጀ የነዳጅ ሥርዓት አበረታች ሥራ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ ነገር ግን የበለጠ ግልጽነትን ለማስፈን ከ300 በላይ ዝርዝርና 47 ጥቅል አገልግሎቶችን በዲጂታል አገልግሎት እንዲሰጡ ተደርጓል ብለዋል፡፡ የመንግሥት መሻትና የሕዝብ ፍላጎት የሚሳካው አገልግሎቶችን ዘመኑን በዋጀ ቴክኖሎጂ መደገፍ ሲቻል መሆኑን በማንሳት፤ የዲጂታል መተግበሪያዎች የዚህ ማሳያዎች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ደስታው መኳንንት (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ባለሥልጣኑ ያለማቸው የዲጂታል መተግበሪያዎች ለተቋም ግንባታ መሠረት ይጥላሉ ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያን የአፍሪካ ብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ ለተጀመረው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ሽግግር ወሳኝ እርምጃ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የነዳጅ አቅርቦት ግብይትና ሥርጭት የተቋማትን አቅም መገንባት የሚያስችል መሆኑን ገልጸው፤ የዲጂታል መተግበሪያው በነዳጅ ዘርፍ 29 አገልግሎቶችን ሙሉ በሙሉ፣ በኢነርጂ ዘርፍ 36 አገልግሎቶችን በከፊል በዲጂታል ቴክኖሎጂ መስጠት ተጀምሯል ብለዋል፡፡
ኤጀንሲው የጀመራቸውን የዲጂታል አሰራሮች አጠናክሮ ይቀጥላል
Jul 28, 2026 145
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 21/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ የጀመራቸውን የዲጂታል አሰራሮች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጸ፡፡ የኤጀንሲውን የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም አስመልክቶ ዋና ዳይሬክተሩ ዮሴፍ ንጉሤ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ በመግለጫቸውም ኤጀንሲው በ2018 በጀት ዓመት ለ1 ነጥብ 5 ሚሊየን ተገልጋዮች 2 ነጥብ 4 ሚሊየን የኩነትና የነዋሪነት አገልግሎቶች መስጠቱን አስታውቀዋል፡፡ በበጀት ዓመቱ የልደት፣ የጋብቻ፣ የፍቺ፣ የሞትና የጉዲፈቻ ምዝገባዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። ወቅታዊ የኩነት ምዝገባ ለስታትስቲክስ፣ ለፖሊሲ ቀረጻና ለአስተዳደራዊ ውሳኔዎች ጠቃሚ የመረጃ ምንጭ መሆኑን ጠቅሰው፤ ዜጎች የልደት ምዝገባቸውን በ90 ቀናት ውስጥ እንዲያከናውኑ ጥሪ አቅርበዋል። ኤጀንሲው የኩነት ምዝገባ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ በጤና ተቋማትና በፍርድ ቤቶች የአንድ መስኮት አሰራርን ማስፋቱን ገልጸዋል። በዚህም 94 በመቶ የወቅታዊ የልደት ምዝገባዎች በጤና ተቋማት በተቋቋሙ የአንድ መስኮት ማዕከላት መከናወናቸውን፤ የፍቺና የጉዲፈቻ ምዝገባዎችም በፍርድ ቤቶች በተቀናጀ አገልግሎት 100 በመቶ መከናወናቸውን ጠቁመዋል። ከአገልግሎት ዘመናዊነት አንጻርም ኤጀንሲው በአካል በመገኘት የሚሰጠውን አገልግሎት ወደ ዲጂታል አሰራር ማሸጋገር መጀመሩን ጠቁመው ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በዚህም የልደት፣ የያላገባ ማስረጃና የመታወቂያ አገልግሎቶች ተገልጋዮች ወደ ቢሮ ሳይመጡ በዲጂታል ካሉበት ሆነው እንዲጠይቁ የሚያስችል ስርዓት መጀመሩን አስታውቀዋል። ኦንላይን አገልግሎቱ ከተጀመረ በኋላ 8 ሺህ 872 ተገልጋዮች ወደ ቢሮ ሳይመጡ አገልግሎት ማግኘታቸውንም ገልጸዋል። ከፋይዳ መታወቂያ ጋር የነዋሪነት መታወቂያን የማስተሳሰር ስራው ተጠናክሮ መቀጠሉንና፤ ይህም የዜጎችን ማንነት በአንድ መለያ ለማረጋገጥና የሐሰተኛ ሰነዶችን አጠቃቀም ለመቀነስ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። በ2018 በጀት ዓመት 1 ሚሊየን 828 ሺህ 846 ተገልጋዮች በኤጀንሲው በኩል የፋይዳ ምዝገባ ማጠናቀቃቸውን፤ ፋይዳ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ 8 ሚሊየን ያህል ተጠቃሚዎች በኤጀንሲው በኩል መመዝገባቸውን ጠቁመዋል። በተጨማሪም 12 ሚሊየን የሚደርሱ የነዋሪነት ሰነዶች በዲጂታል ስርዓት እንዲቀመጡ መደረጋቸውን ገልጸው ይህም የሰነድ መጥፋትንና የመረጃ አያያዝ ችግሮችን በመቀነስ የአገልግሎት ጥራትን አሻሽሏል ብለዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት ወቅታዊ የኩነት ምዝገባ በተከታታይ እያደገ መምጣቱንና ይህም የአገልግሎቱ ተደራሽነትና ቅልጥፍና መሻሻሉን እንደሚያመላክት ገልጸዋል። በ2019 በጀት ዓመት የሞት ምዝገባን ወደ ጤና ተቋማትና ሌሎች የማህበረሰብ ተቋማት ማስፋት፣ የመታወቂያ ህትመትን ወደ ወረዳ ማውረድና የኦንላይን አገልግሎቱን ማስፋት ዋና ዕቅዶች መሆናቸውን ጠቁመዋል። ኤጀንሲው በ2018 በጀት ዓመት ባስመዘገበው የአገልግሎት አፈጻጸም ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እውቅና እና ሽልማት ማግኘቱንም ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርስቲ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መንግስት ጋር በመተባበር ያስገነባው ዘመናዊ የላቀ ላቦራቶሪ የሀገራቱን ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ መሸጋገሩን የሚያሳይ ነው
Jul 26, 2026 283
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 19/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርስቲ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መንግስት ጋር በመተባበር ያስገነባው ዘመናዊ የላቀ ላቦራቶሪ የሀገራቱ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ መሸጋገሩን የሚያሳይ ነው ሲሉ የመከላከያ ሚኒስትሯ ኢንጅነር አይሻ መሀመድ ገለጹ። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መንግስት ጋር በመተባበር ያስገነባውን የማሰልጠኛ እና የምርምር ዘመናዊ የላቀ ላብራቶሪ ስራ አስጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሀግብሩ የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) ፤የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ብርጋዴር ጀነራል ከበደ ረጋሳ፣የመከላከያ ሰራዊት ጀነራል መኮንኖች፣የተባበሩት አረብ ኢመሬትስ ተወካዮች እንዲሁም የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች ተገኝተዋል። ላቦራቶሪው በ20 ሺህ 850 ካሬ ሜትር መሬት ላይ የተገነባ ሲሆን በውስጡ ለስልጠና እና ምርምር የሚያገለግሉ ቁሳቁሶች የተሟሉለት መሆኑ ተገልጿል። ላቦራቶሪው በውስጡ የሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ የሳይበር፣ የኤሌክትሪክ ሀይል፣የአውቶሜሽን፣የኮሙኒኬሽን እና ኤሌክትሮኒክስ፣የነርሲንግ ሲሙሌሽን ላብራቶሪዎች በውስጡ ማካተቱ ተመላክቷል። በተጨማሪም ላቦራቶሪው ዘመናዊ የሶላር ስርዓት እና ዘመናዊ መሳሪያዎች የተገጠሙለት መሆኑ ተመላክቷል። የመከላከያ ሚኒስትሯ ኢንጅነር አይሻ መሀመድ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ በላቦራቶሪው መሰረተ ልማቱ የረቀቁ ቴክኖሎጂዎችን ጥቅም ላይ ማዋል ብቻውን በቂ አይደለም ብለዋል። ይልቁንም እውቀትን ወደ ሙያዊ ብቃት፣ምርምርን ወደ ፈጠራ እንዲሁም ፈጠራን ለሀገራችን አገልግሎት ወደሚውሉ ተግባራዊ መፍትሄዎች የሚቀይር አዲስ የትምህርት የሳይንስ እና ተቋማዊ አቅም የተከፈተበት ታላቅ አጋጣሚ መሆኑን ገልጸዋል። የዚህ የልህቀት ምእራፍ መሰረት በኢትዮጵያ እና በተባበሩት አረብ ኤሜሬቶች መካከል ዘመናትን የተሻገረ ወዳጅነት እና ስትራቴጂካዊ አጋርነት መሆኑን ገልጸዋል። ይህ ታሪካዊ ወዳጅነት ቀደም ሲል ከነበሩት ዲፕሎማሲያዊና ኢኮኖሚያዊ ትብብሮች ባሻገር አሁን ላይ የሁለቱን ሀገራት ሀገራዊ ደህንነት፣ቴክኖሎጂያዊ ሽግግርና የተቋማትን ዘመናዊነት ወደሚያጎለብት የላቀ ምእራፍ መሸጋገሩን ጠቁመዋል። የላቦራቶሪ ማእከሉ በቁሳቁስ ድጋፍ ደረጃ ብቻ ሳይሆን በእውቀት ሽግግር ፣በሳይንሳዊ ምርምር እና በሀገር በቀል የቴክኖሎጂ አቅም ግንባታ ትውልድን የሚቀርጽ መሆኑን ጠቁመዋል። ላቦራቶሪው የመከላከያ ሰራዊቱን ሁለንተናዊ የዘመናዊነት ጉዞ የሚያፋጥን የተቋሙን የቴክኖሎጂና ምርምር መሰረት የሚያጎለብት እና የወደፊት ሀገራዊ ደህንነት በጽኑ መሰረት ላይ የሚጥል ታላቅ እርምጃ መሆኑን አመላክተዋል፡፡
የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ከተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መንግስት ጋር በመተባበር ያስገነባው ዘመናዊ የላቀ ላቦራቶሪ የሀገራቱን ዘላቂ ወዳጅነት የሚያሳይ ታሪካዊ ምልክት ነው
Jul 26, 2026 267
አዲስ አበባ ፤ሐምሌ 19/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ከተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መንግስት ጋር በመተባበር ያስገነባው ዘመናዊ የላቀ ላቦራቶሪ የሀገራቱን ዘላቂ ወዳጅነት እና ስትራቴጂያዊ አጋርነትን የሚያሳይ ታሪካዊ ምልክት መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ብርጋዴር ጄኔራል ከበደ ረጋሳ ገለጹ። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ከተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መንግስት ጋር በመተባበር ያስገነባውን የማሰልጠኛ እና የምርምር ዘመናዊ የላቀ ላቦራቶሪ ስራ አስጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሀግብሩ የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሀመድ፣ የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር)፣የመከላከያ ሰራዊት ጄኔራል መኮንኖች፣የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ተወካዮች እንዲሁም የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች ተገኝተዋል። ላቦራቶሪው በ20 ሺህ 850 ካሬ ሜትር ላይ የተገነባ ሲሆን በውስጡ ለስልጠና እና ምርምር የሚያገለግሉ ቁሳቁሶች የተሟሉለት መሆኑ ተገልጿል። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ብርጋዴር ጄኔራል ከበደ ረጋሳ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ፕሮጀክቱ በእውቀት፣ በፈጠራና በሰው ኃብት ላይ የሚደረግ ኢንቨስትመንት ለዘላቂ ልማትና ለብሔራዊ ደህንነት መሠረት መሆኑን የሚያንጸባርቅ ነው ብለዋል። ለፕሮጀክቱ ስኬት አስተዋጽኦ ላበረከቱት የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መንግሥት ላሳየው ድጋፍና ቁርጠኝነት ምስጋና አቅርበዋል። ይህም በሁለቱ ወንድማማች ሀገራት መካከል ያለውን ጠንካራ ግንኙነትና የጋራ የልማት ራዕይ የሚያሳይ ተጨማሪ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። ላቦራቶሪው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የሳይበር ደህንነት፣ የመገናኛ ምህንድስና፣ የአውቶሜሽንና የቁጥጥር ሥርዓቶች፣ የኃይል ምህንድስና፣ የ3ዲ ዲዛይን፣ የፕሮቶታይፕ ልማት እና የነርሲንግ ሲሙሌሽን ዘርፎችን የሚያካትቱ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸው መገልገያዎችን መያዙን ተናግረዋል። ይህም ለከፍተኛ ትምህርት፣ ለሳይንሳዊ ምርምር፣ ለቴክኖሎጂ ፈጠራ፣ ለምርት ልማት፣ ለምህንድስና መፍትሔዎችና ለቴክኖሎጂ ሽግግር የተቀናጀ መድረክ እንደሚፈጥር አንስተዋል። በተጨማሪም ማዕከሉ በዩኒቨርሲቲዎች፣ በኢንዱስትሪ፣በመንግሥት ተቋማትና በዓለም አቀፍ አጋሮች መካከል የምርምርና የፈጠራ ትብብርን የሚያጠናክር መሆኑን ጠቁመዋል። የማዕከሉ ስኬት በተገጠሙ መሣሪያዎች ሳይሆን በሚያፈራቸው ብቁ ባለሙያዎች፣ በሚያመነጨው ምርምር፣ በሚፈጥረው ፈጠራና ለሀገር የሚያበረክተው ተጨባጭ አስተዋጽኦ እንደሚለካ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ዘመናዊ የማሰልጠኛ እና የምርምር የላቀ ላቦራቶሪ በይፋ ስራ ጀመረ
Jul 26, 2026 201
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 19/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ከተባበሩት አረብ ኢምሬቶች (UAE) መንግስት ጋር በመተባበር ያስገነባውን ዘመናዊ የማሰልጠኛ እና የምርምር የላቀ ላቦራቶሪ በይፋ ስራ አስጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሐመድ፣ የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) ፣ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ብርጋዴር ጀነራል ከበደ ረጋሳ፣ የመከላከያ ሰራዊት ከፍተኛ ጀነራል መኮንኖች፣ የተባበሩት አረብ ኢምሬቶች ተወካዮች እንዲሁም የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች ተገኝተዋል። ላቦራቶሪው በ20 ሺህ 850 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ ሲሆን፣ ለላቀ ስልጠና እና ምርምር የሚያስፈልጉ ዘመናዊ ቁሳቁሶች ሙሉ በሙሉ የተሟሉለት ነው። በውስጡ የሰው ሰራሽ አስተውሎት፣የሳይበር፣የኤሌክትሪክ ኃይል፣የአውቶሜሽን፣ የኮሙኒኬሽን እና ኤሌክትሮኒክስ እንዲሁም የነርሲንግ ሲሙሌሽን ላቦራቶሪዎችን አካቷል። ህንፃዎች በተለየ መልኩ ዘመናዊ የሶላር የኃይል ስርዓትና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች የተገጠሙለት ነው። ማዕከሉ የተለያዩ የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂ እና የመከላከያ ምርምር ዘርፎችን በአንድ ላይ የሚያገናኝ ዘመናዊ የእውቀት ማዕከል መሆኑም ተጠቁሟል፡፡ ለዩኒቨርሲቲው ወደ ተግባራዊ ምርምርና ፈጠራ ይበልጥ ለመሸጋገር ትልቅ እምርታን የሚፈጥር ነው ተብሏል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ማዕከሉ ለመከላከያ ዘርፍ ብቻ ሳይሆን ለሀገሪቱ አጠቃላይ የቴክኖሎጂ፣ የኢንዱስትሪ፣የጤና እና የሳይንስ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተመላክቷል።
በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዘርፍ የዲጂታል ሽግግርን የሚያፋጥን የሰው ኃይል እየተገነባ ነው
Jul 25, 2026 448
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ)፦ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዘርፍ የዲጂታል ሽግግርን የሚያፋጥን የሰው ኃይል እየተገነባ መሆኑን የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ለመጀመሪያ ጊዜ በሰው ሠራሽ አስተውሎት የሰለጠኑ ስታርት አፖችን አስመርቋል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ዲጂታል ሽግግር ጠንካራ የሰው ኃይል አቅም እንዲሁም አስተማማኝ መሠረተ ልማቶችን ይጠይቃል። ኢንስቲትዩቱ ከተቋቋመ በአጭር ጊዜ ውስጥ ሀገሪቱን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዘርፍ ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ውጤቶች መገኘታቸውን ተናግረዋል። በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዘርፍ በአፍሪካ የመጀመሪያው የሰው ሠራሽ አስተውሎት ፖሊሲና ስትራቴጂ መቀረጹን፣ ችግር ፈቺ ውጤቶች መመረታቸውን፣ ለአለም ገበያ ብቁ የሆኑ ዲጂታል ባለሙያዎችን ማፍራት መቻሉን፣ የሰው ሠራሽ አስተውሎት መሠረተ ልማት ዝርጋታና ሌሎች ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቅሰዋል። በሁሉም ዘርፎች በተለይም ቅድሚያ በሚሰጣቸው የፍትህና አስተዳደር፣ ስማርት ኮርት (ዘመናዊ ፍርድ ቤት)ና ስማርት ፖሊስ ጣቢያ፣ ጤና፣ የሕዝብ አገልግሎትና በሌሎች ዘርፎች በAI የታገዙ ቴክኖሎጂዎች በስፋት ሥራ ላይ መዋላቸውን ገልጸዋል። በዘርፉ ለተገኘው ስኬት በስታርታፕ፣ ሰመር ካምፕ፣ በትምህርት ቤቶች፣ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና በሌሎች ተቋማት የሰው ኃይል ልማት ጠንካራ የአቅም ግንባታ ሥራዎች በመከናወኑ ነው ብለዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የሰለጠኑት ተመራቂዎች የዲጂታል ኢኮኖሚውን ለማንቀሳቀስ ዝግጁ የሆኑ፣ የተፈተሹ፣ ሥራ ላይ የዋሉና በገበያው ሊስፋፉ የሚችሉ ውጤቶች ማቅረባቸውን ገልጸዋል። እነዚህ ውጤቶች የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ወደ ተግባር መሸጋገሩን እንደሚያሳዩ ተናግረዋል። በዕለቱ በተዘጋጀው አውደ-ርዕይ ሰልጣኞቹ በጤና፣ በትምህርት፣ በትራንስፖርት፣ በቋንቋ ቴክኖሎጂ፣ በስማርት ሲቲ፣ በፋይናንስ እና በሰብዓዊ ልማት ዘርፎች የሠሯቸውን ችግር ፈቺ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ለዕይታ አቅርበዋል።
ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት የነገውን ዓለም ታሳቢ በማድረግ ብሔራዊ ጥቅሟን የሚያስጠብቅ የሰው ኃይል እያፈራች ነው
Jul 25, 2026 226
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት የነገውን ዓለም ታሳቢ በማድረግ ብሔራዊ ጥቅሟን የሚያስጠብቅ የሰው ኃይል እያፈራች መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ባለፉት ስድስት ወራት በሰው ሠራሽ አስተውሎት ያሰለጠናቸውን ስታርታፖች በይፋ አስመርቋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንዳሉት፤ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የነገውን ዓለም ጉዞ እየቃኘና እየወሰነ ይገኛል። ኢትዮጵያም ይህንን ዕድል ለብሔራዊ ጥቅም ለማዋልና የነገውን ዓለም ጉዞ በብቃት ለመቃኘት ተተኪውን ትውልድ በዘርፉ የማብቃትና የማንቃት ተግባራትን እያከናወነች መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ሰልጥነው ለምረቃ የበቁት ስታርታፕ ሰልጣኞችም ትልቅ ማሳያ መሆናቸውን ተናግረዋል። መመረቅ የመጨረሻ መዳረሻ ሳይሆን ለረጅም ጉዞ የመጀመሪያ ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በስልጠና ቆይታቸው ዕውቀትና በራስ መተማመን አቅም መገንባታቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም የፈጠራ ሥራዎቻቸውን በታማኝነት በማሳደግ ለሀገር የሚጠቅሙ መፍትሔዎችን እንዲያቀርቡና ኢትዮጵያን በዘርፉ ተወዳዳሪ የሚያደርጉ የቴክኖሎጂ አምባሳደሮች እንዲሆኑ አስገንዝበዋል። መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማትም የኢንስቲትዩቱን አርዓያነት ያለው ጉዞ እንዲከተሉ ጥሪ አቅርበዋል። ኢትዮጵያ በስታርታፕ ልማት ለራሷ አልፎ ለመላው አፍሪካውያን ወጣቶች የምትተርፍ እንድትሆን ቀጣይነት ያለው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በመጨረሻም ለተመራቂ ስታርታፖች መልካምና ስኬታማ የሥራ ዘመን ተመኝተዋል። በዕለቱ በተዘጋጀው አውደ-ርዕይ ሰልጣኞቹ በጤና፣ በትምህርት፣ በትራንስፖርት፣ በቋንቋ ቴክኖሎጂ፣ በስማርት ሲቲ፣ በፋይናንስ እና በሰብዓዊ ልማት ዘርፎች የሠሯቸውን ችግር ፈቺ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ለዕይታ አቅርበዋል።
የሀገራችንን መዳረሻ በራሳችን ዕውቀትና ጥበብ እንቀርጻለን - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Jul 25, 2026 182
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የወደፊት ዕጣ ፈንታዋንና መዳረሻዋን ሌሎችን ጣልቃ ሳታስገባ በራሷ ዕውቀት እና ጥበብ ትቀርጻለች ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት አማካኝነት በሀገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያዎቹን የኤአይ ስታርትአፕ ሠልጣኞች በሳይንስ ሙዚየም ዛሬ በድምቀት ማስመረቃቸውን ጠቁመዋል። እኛ የወደፊቱን ዕጣ ፈንታችንን እና መዳረሻችንን ሌሎች እንዲወስኑ አንጠብቅም አንፈቅድም፤ ይልቁንም በሀገራችን ጥበብ፣ በራሳችን ዕውቀት እንቀርጸዋለን ሲሉ ተናግረዋል። ይህም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለዘርፉ የሰጡት ልዩ ትኩረትና የቅርብ ክትትል ፍሬ፣ እንዲሁም ሀገራችን በልጆቿ ጥረት ያስመዘገበችው ትልቅ የስኬት ምዕራፍ ማሳያ ነው ብለዋል። ወጣት ፈጣሪዎች በጤና፣ በትምህርት፣ በትራንስፖርት፣ በስማርት ሲቲ፣ በፋይናንስና በሌሎችም ዘርፎች የተሠማሩ መሆናቸውን አብራርተዋል። በቴክኒክና የምርት ልማት ክሂሎት፣ ትክክለኛ ችግር ፈቺ የቢዝነስ አስተሳሰብ፣ ደረጃውን የጠበቀ የኤአይ ወርክሾፕ፣ የክላውድ ዳታ ማዕከል እና ከፍተኛ የኮምፒዩቲሽናል ሪሶርስ ድጋፍ ማግኘታቸውንም ነው የገለጹት። አንድ ስታርትአፕ ሲደገፍ የላቀ ቴክኖሎጂ እንዲሁም ለብዙዎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል፤ መንግሥታችን ለዚህ ትኩረት ሰጥቷል። የዛሬ ተመራቂዎችም ተጨባጭ ማሳያ ናቸው ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።
በኦሮሚያ ክልል አገልግሎቶችን ከብልሹ አሰራር የፀዱ ማድረግ የሚያስችል ሪፎርም እየተተገበረ ነው
Jul 25, 2026 162
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ለሕብረተሰቡ የሚሰጡ አገልግሎቶችን ከሙስና እና ብልሹ አሰራር የፀዱ ማድረግ የሚያስችል ሪፎርም ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ ተናገሩ። ''የአገልግሎት እና አስተዳደር ሪፎርም ለሁለንተናዊ ብልጽግና'' በሚል መሪ ሀሳብ የኦሮሚያ ክልል የመንግስት አገልግሎት እና አስተዳደር ሪፎርም ትግበራ ይፋ ማድረጊያ መርሃ ግብር በቢሾፍቱ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ፣ የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ሀይሌ (ዶ/ር)፣ የክልሉ የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ኮከቤ ዲዳ፣ የመንግስት ከፍተኛ የቢሮ ኃላፊዎችና አመራሮች ተገኝተዋል። የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፣ የአገልግሎት አሰጣጥን ግልጽ እና ተጠያቂነት ያለው በማድረግ የሙስና እና የብልሹ አሰራር ችግሮችን መፍታት የሚያስችል ሪፎርም እየተተገበረ ይገኛል። ከዚህ ውስጥም በክልሉ ከቀበሌ ጀምሮ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን የተሳለጠ ማድረግ የሚያስችል አሰራር ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የተለያዩ አልግሎቶችን በዲጂታል ስርዓት በመደገፍ የህዝቡን እንግልት፣ ጊዜና ወጪ በመቆጠብ ቀልጣፋ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። በየደረጃው የሚገኘው የክልሉ አመራርና ሰራተኛም ለህዝብ የሚሰጠውን አገልግሎት የተገልጋዩን እንግልት ለመቀነስ ሰፊ ጥረት እያደረጉ እንደሚገኙም አመልክተዋል። በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥ እንዲኖር የማድረግ ስራ ልዩ ትኩረት እንደሰጠውም ነው የገለጹት። በአሁኑ ወቅትም የመንግስት ሰራተኞች አቅምን የማሳደግ፣ አዎንታዊ የስራ ባህልን መገንባት እና የዜጎችን እርካታ ማረጋገጥ የሚያስችል ስራዎች ተግባራዊ እየተደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል። በለውጡ ዓመታት በክልሉ የተለያዩ የሪፎርም ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አመልክተው በአዲሱ በጀት ዓመትም የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም በተሟላ መልኩ የሚተገበር ይሆናል ብለዋል። የክልሉ የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ኮከቤ ዲዳ በበኩላቸው፣ የመንግሥት መስሪያ ቤቶችን አሰራር የማዘመንና የሰው ኃይሉን አቅም መገንባት የሚያስችል አሰራር እየተዘረጋ መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም የአገልግሎት አሰጣጥን በዲጂታል መንገድ የማደራጀት ስራ እየተሰራ ሲሆን ከዚህ ውስጥም 58 የመሶብ አንድ ማዕከል መስጫ ተቋማት አገልግሎት መጀመራቸውን ጠቅሰዋል።
በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በማስፋት የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 25, 2026 193
አሶሳ፤ ሐምሌ 18/2018 (ኢዜአ)፡- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በማስፋት የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን ትኩረት መስጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክርቤት 6ኛ ዙር 5 ዓመት 3ኛ የሥራ ዘመን 5ኛ መደበኛ ጉባኤ እየተካሄደ ነው። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን በጉባኤው የክልሉን የ2018 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት አቅርበዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በወቅቱ እንዳስታወቁት የሲቪል ሰርቪስ አገልግሎት ዘመናዊነትን የተላበሰ እና ከህዝብ ቅሬታ የፀዳ ለማድረግ ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተከናወኑ ነው። በክልሉ የቤጉ መሶብ እና የአሶሳ መሶብ አንድ ማዕከላት አገልግሎት ከብልሹ አሰራር የፀዳ አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን ገልፀው፤ ማዕከላቱ ከ16 ተቋማት የተለዩ 83 አገልግሎቶችን ተደራሽ እያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። በማዕከላቱ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ39ሺህ በላይ ዜጎች የአገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁመው በዚህም የላቀ የተገልጋዮች እርካታ ደረጃ ተመዝግቧል ብልዋል። በክልሉ የመሶብ አገልግሎትን ለማስፋፋት በተያዘው ዕቅድ መሠረት በባምባሲ፣ ከማሺ እና ግልገል በለስ ከተሞች የተገነቡ ማዕከላት በዚህ ወር መጨረሻ ወደ ስራ እንደሚገቡ አስታውቀዋል። የክልሉ መንግስት በአገልግሎት አሰጣጥና በመልካም አስተዳደር ላይ የሚነሱ የህዝብ ቅሬታዎችን ለመፍታት በተቋማት ደረጃ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም እያከናወነ መሆኑንም አንስተዋል።
የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ ለውጥ መዲናዋን ከአህጉራዊ የቱሪስት መሸጋገሪያነት ወደ የአፍሪካ የቱሪዝም ማዕከልነት አሳድጓታል - ኮሚሽነር ሁንዴ ከበደ
Jul 25, 2026 205
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ ለውጥ መዲናዋን ከአህጉራዊ የቱሪስቶች መሸጋገሪያነት ወደ የአፍሪካ የቱሪዝም ማዕከልነት ማሳደጉን የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽነር ሁንዴ ከበደ ገለጹ። ፐልስ ኦፍ አፍሪካ የሚዲያ ተቋም (POA) እና የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽን በቱሪዝም ዘርፍ በቅርበት መስራት የሚያስችል የትብብር ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱን የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሰይፈ ደርቤ እና የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሁንዴ ከበደ ፈርመውታል። ኮሚሽነር ሁንዴ ከበደ በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ እንደገለጹት፤ ስምምነቱ ቀደም ሲል በነበረው የትብብር የሥራ ግንኙነት ላይ የላቀ እሴት በመጨመር ወደ ከፍተኛ የአጋርነት ደረጃ የሚያሸጋግር ነው። ስምምነቱ የአዲስ አበባን ሁለንተናዊ የቱሪዝም እመርታ በሰፊው በማስተዋወቅ የቱሪዝም እንቅስቃሴን ለማጠናከርና የዘርፉን ዕድገት ለማፋጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል። አዲስ አበባ በቅርብ ዓመታት በርካታ የቱሪዝም መዳረሻዎችና ዘመናዊ መሠረተ ልማቶች የተገነቡባት አፍሪካዊት የከተሜነት አብነት እየሆነች እንደሚገኝም ተናግረዋል። ለአብነትም በኮንፍረንስ ቱሪዝም አዲስ አበባ የአህጉሪቱ ቀዳሚ ማዕከል መሆኗን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 221 ዓለም አቀፍ ጉባኤዎችን በስኬት ማስተናገድ እንደተቻለ አስረድተዋል። የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ ለውጥ መዲናዋን ከአህጉራዊ የቱሪስት መሸጋገሪያነት ወደ የአፍሪካ የቱሪዝም ማዕከልነት እንዳሳደጋት ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። የአዲስ አበባን የልማትና የቱሪዝም እመርታዎች በሰፊው ለማስተዋወቅ፣ ገጽታ ለመገንባትና የቱሪዝም ፍሰትን ለማሳደግ ሰፊ ልምድ ካላቸው የሚዲያ ተቋማት ጋር መተባበር ወሳኝ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሰይፈ ደርቤ እንደተናገሩት፤ ኢዜአ ብሔራዊ ጥቅምን በማስቀደም፣ የሀገር ገጽታን በመገንባትና የሕዝቦችን አብሮነት በማጠናከር በኩል በትኩረት እየሠራ ነው። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት በታሪክ ውስጥ የአፍሪካ ሕዝቦች ከቅኝ ግዛት ነፃ እንዲወጡ በመረጃና በዜና ድጋፍ ገንቢ ሚና የተጫወተ አንጋፋ ተቋም መሆኑንም አስታውሰዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዕሳቤ መሠረት የቅድመ አያቶችን የፓን አፍሪካኒዝም ርዕይ ለማስቀጠል አፍሪካውያን የራሳቸውን ታሪክ በራሳቸው ድምጽ የሚናገሩበት ፐልስ ኦፍ አፍሪካ (POA) የሚዲያ ተቋም ወደ ሥራ መግባቱን አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅትም ፐልስ ኦፍ አፍሪካ (POA) የሚዲያ ተቋም የአፍሪካን የተዛቡ ትርክቶች በማረምና አህጉሪቱን በተጨባጭ እውነታዎች በማቅረብ የተሻለ ዓለም አቀፍ ገጽታ ለመገንባት እየሠራ ነው ብለዋል። በዚህም የአዲስ አበባን የቱሪዝም ፀጋዎችና የልማት እመርታዎች ለሀገር ውስጥና ለውጭ ታዳሚዎች በሰፊው በማስተዋወቅ ከፍተኛ ሚና እንደሚወጣ ተናግረዋል። የትብብር ስምምነቱም የመዲናዋን ገጽታ ከማስተዋወቅ ባሻገር አፍሪካውያን የአዲስ አበባን የልማት ሥራዎች እንዲያውቁ በማስቻል የቱሪዝም ፍሰትን ለማሳደግ ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል። በቀጣይም የትብብር ስምምነቱን ወደ ተጨባጭ ውጤት በመቀየር በሀገር ውስጥና በዓለም አቀፍ ቋንቋዎች በትኩረት በመስራት የአዲስ አበባን የቱሪዝም አቅም ለዓለም ለማስተዋወቅ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
በክልሉ የግብር አከፋፈል ስርአቱን ቀልጣፋና አስተማማኝ ለማድረግ እየተሰራ ነው
Jul 24, 2026 263
ባህርዳር፤ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፦ የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ የግብር አከፋፈል ስርአቱን በቴሌ ብር በማድረግ ቀልጣፋና አስተማማኝ ስርአት ለመዘርጋት እየሰራ መሆኑን አስታወቀ። የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ የግብር አከፋፈል ስርአቱን በቴሌ ብር ለማድረግ የሚያስችል ስምምነት ኢትዮ ቴሌኮም ጋር ዛሬ ማምሻውን ተፈራርሟል። የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ሃላፊ መንገሻ ፈንታው (ዶ /ር) በወቅቱ እንደገለጹት፥ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ90 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ በራስ አቅም የመልማት ባህልን በማጎልበት አበረታች ውጤት ተገኝቷል። በአዲሱ በጀት ዓመትም የግብር ስርአቱን ዲጅታላይዝ በማድረግ ግልጽ፣ ቀልጣፋና ተአማኒነት ያለው የግብር ስርአት ለመገንባት ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲና ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር የተደረሰው ስምምነትም ወደ ኢ-ታክስ ሲስተም የገቡ 420 ሺህ የደረጃ “ለ” ግብር ከፋዮችን ጨምሮ የደረጃ "ሀ" እና "ሐ" ግብር ከፋዮች ግብራቸውን በቀላሉና በፍጥነት ባሉበት ቦታ ሆነው እንዲከፍሉ የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል። በተጨማሪም የግብር ስርአቱን ተደራሽ ለማድረግና በዘርፉ የሚስተዋለውን ብልሹ አሰራር ለማስቀረት የሚያስችል መሆኑንም ጠቁመዋል። በኢትዮ ቴሌኮም ችፍ የሞባይል ባንኪንግ ቢዝነስ ኦፊሰር አቶ ቡሩክ አዳነ በበኩላቸው፥ ከክልሉ ገቢዎች ቢሮ ጋር የተደረገው ስምምነት ዲጅታል 2030ን እውን ለማድረግ የሚያስችል ነው ብለዋል። ቢሮው ባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ያበለጸገውን የኢ-ታክስ ሲስተም ከቴሌ ብር ጋር በማስተሳሰር ደንበኞች በቀላሉ ግብራቸውን የሚከፍሉበት ስርአት ለመገንባት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። የግብር ክፍያውን በቴሌ ብር ለማድረግም በዩኒቨርሲቲው የበለጸገውን ሲስተም ከቴሌብር ጋር እንዲናበብ በማድረግ፣አሰራሩን በመፈተሽና የደህንነት ጉዳዮችን የማረጋገጥ ስራ ቀድሞ ማጠናቀቁን ተናግረዋል። ደንበኞችም ከገቢዎች ቢሮ የሚሰጠውን የመክፈያ ኮድ በማስገባት ግብራቸውን በቴሌብር በቀላሉ፣ በፍጥነትና አስተማማኝነት ባለው መንገድ እንዲከፍሉ የሚያስችል ነው ብለዋል። አያይዘውም ኩባንያው ቴሌብር የሚጠቀሙ ደንበኞችን ቁጥር 60 ነጥብ 5 ሚሊየን ማድረሱን ጠቁመው ባለፉት አምስት ዓመታትም 9 ትሪሊዮን የሚጠጋ የገንዘብ ዝውውር ማድረግ መቻሉን አውስተዋል። የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት መንገሻ አየነ በበኩላቸው፥ ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር፣ ምርምር፣ ማህብረሰብ አገልግሎትና ቴክኖሎጂ ሽግግር ባሻገር ከተቋማት ጋር በቅንጅት ለሀገር እድገት የሚበጁ ተግባራትን አያከናወነ ይገኛል ብለዋል። ከክልሉ ገቢዎች ቢሮ ጋር በመተባበርም የኢ-ታክስ ፕሮጀክትን በማልማት የዘርፉን ችግር ለመፍታት መስራቱን ጠቁመው፥ አሁን ላይ ከኢትዮ ቴሌኮም ጋር የተደረሰው ስምምነት የኢ-ታክስ ሲስተሙን ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ነው ሲሉ አክለዋል። ማምሻውን በተካሄደው ስምምነት ላይም የቢሮው የማኔጅመንት አበላት፣ የኢትዮ-ቴሌኮም የስራ ሃላፊዎች፣ የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ አመራሮች ተገኝተዋል።
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የተቀላጠፈ አገልገሎት እንድናገኝ አስችሏል
Jul 24, 2026 180
ቦንጋ፤ ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፦ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ያልተገባ ወጪንና እንግልትን በማስቀረት የተቀላጠፈ አገልገሎት እንድናገኝ እያስቻለ ነው ሲሉ በቦንጋ ከተማ የማዕከሉ ተገልጋዮች ተናገሩ። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግ ማህበረሰቡ በአቅራቢያው ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኝ በትኩረት እየተሰራ መሆኑ ተጠቁሟል። በክልሉ ከሚገኙ ስድስት መሶብ የአንድ ማዕከላት መካከል አንዱ በሆነው የቦንጋ ማዕከል ሲገለገሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው ዜጎች ከእንግልት የፀዳ ቀልጣፋና ግልፅ አገልግሎት እያገኙ መሆኙን ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል ነስረዲን ኑሩ እና ወጣት ሀይማኖት ታምሩ፤ በማዕከሉ አዲስ ንግድ ፈቃድን በአጭር ደቂቃና ፍጥነት ያለምንም እንግልት ማውጣታቸውን ነው የገለጹት። ይህም ከዚህ ቀደም የነበረውን የተንዛዛ አሰራር በማስቀረት ጊዜያቸውን በአግባቡ መጠቀም እንዳስቻላቸው ጠቁመው፣ በቀጣይ ወደ ማዕከሉ ያልገቡ ተቋማትን በማካተት አገልግሎቱን ማስፋት እንደሚገባም ነው የተናገሩት። ከዚህ ቀደም የተለያዩ አገልግሎቶችን ለማግኝት ብዙ ምልልሶችና እንግልት እንደሚገጥመው ያነሳው ደግሞ ወጣት እምሩ መሸሻ ሲሆን፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ በማዕከሉ ያለምንም እንግልት አገልግሎት ማግኘቱን ነው የተናግረው። አሰራሩ ከእጅ መንሻ የፀዳ ግልፅና ፈጣን በመሆኑ ከዚህ ቀደም የነበሩ እሮሮዎችን በመፍታት እርካታን የጨመረ በመሆኑ አገልግሎቱን የማስፋት ስራ መጠናከር አለበት ነው ያለው። የቦንጋ መሶብ የአንድ ማዕከል አልግሎት ዋና ስራ አስኪያጅ አወል አባገሮ ተበታትነው ይሰጡ የነበሩ አገልግሎቶችን በአንድ ማዕከል በመሰብሰብ ለህብረተሰቡ ፈጣን፣ ግልፅ እና ወጪ ቆጣቢ አገልግሎት ለመስጠት እየተሰራ ነው ብለዋል። በማዕከሉ በድምሩ 8 የፌዴራል፣ የከተማ አስተዳደር እና የዞን ተቋማት ተለይተው 44 አገልግሎቶች በአንድ ማዕከል እየተሰጡ ሲሆን በቀጣይ አገልግሎቱን የማስፋት ስራ ይሰራል ብለዋል። የማዕከሉ ባለሙያዎችም የአገልጋይነት መንፈስ ተላብሰው አገልግሎት እየሰጡ በመሆኑ የተገልጋዮች ቁጥር ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ መምጣቱን ጠቁመዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና አስተባባሪ አስራት አዳሮ በበኩላቸው፣ በመሶብ የአንድ ማዕከል የሚሰጡ አገልግሎቶች በተለይ ብልሹ አሰራሮችን ማስቀረት የሚያስችሉ ናቸው። በመጀመሪያ ምዕራፍ የተገነባው የክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እስካሁን ከ36 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አገልግሎት መስጠቱን ተናግረዋል። ይህን ለማስፋት በተሰጠው ትኩረት አምስት ተጨማሪ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎቶች ተመርቀው ወደ ስራ መግባታቸውን ነው ያነሱት። በአዲሱ በጀት ዓመትም ተጨማሪ 15 መሶብ የአንድ ማዕከላትን የመገንባት ስራ መጀመሩን ጠቁመው፣ ይህም ህብረተሰቡ ከስራው ሳይነጠል በአቅራቢያው ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት በአንድ ቦታ ማግኘት ያስችለዋል ብለዋል።
በመዲናዋ ዘመኑን የዋጁ የክህሎትና የቴክኖሎጂ ልማት ስራዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 24, 2026 329
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፡- በመዲናዋ ዘመኑን የዋጁ የክህሎትና የቴክኖሎጂ ልማት ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዛሬው እለት በከተማዋ የመጀመሪያ የሆነውን የስማርት ፖሊቴክኒክ ግንባታን በለሚ ኩራ ከፍለ ከተማ ተገኝተው በይፋ አስጀምረዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት፥ የስማርት ፖሊቴክኒክ ግንባታው ወጣቶችን በክህሎት በማልማት የሀገርን እድገት ለማፋጠን ያለመ ነው ብለዋል። ባለፉት የለውጥ አመታት በመዲናዋ ወጣቶች የክህሎትና የቴክኖሎጂ ልማት ላይ ሰፊ ስራ ሲሰራ መቆየቱን ጠቁመዋል። እነዚህ በክህሎትና በቴክኖሎጂ የበቁ ወጣቶች አሁን ላይ ከራሳቸውና ከቤተሰቦቻቸው አልፈው በሀገር ሁለንተናዊ እድገት ላይ የበኩላቸውን አሻራ እያሳረፉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። አሁን ላይ ወጣቶችን ዘመኑ በደረሰበት የቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት ልክ የማብቃት ስራም ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። አዲሱ ስማርት ፖሊቴክኒክ የጀርመንን የቴክኒክና ሙያ ልምድ መነሻ በማድረግ፣ በከተማዋ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚገነባና ትውልድ ተሻጋሪ እውቀት የሚገበይበት ማዕከል መሆኑን ጠቅሰዋል። ኮሌጁ ወጣቶች እውቀትን የሚታጠቁበት፣አዕምሮ እና የሚሰሩ እጆች ተጣጥመው ሀሳብ የሚያፈልቁበት መሆኑን ገልጸዋል። ኮሌጁ በአመት በርካታ አዳዲስ ሰልጣኞችን የመቀበል አቅም እንደሚኖረው ጠቁመው፤ በዘመናዊ ማኑፋክቸሪንግ፣ በአውቶሞቲቭ፣ በኤሌክትሮኒክስ፣ በኮሙኒኬሽንና በቴክስታይል ቴክኖሎጂ መስኮች ያሰለጥናል ብለዋል። ፕሮጀክቱ በተያዘለት ጊዜ፣ በጀትና ጥራት ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ ከተማ አስተዳደሩ በቅርበት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ስራና ክህሎት ቢሮ ሃላፊ ሚሊዮን ማቲዎስ በበኩላቸው፤ የሚገነባው ኮሌጅ ወጣቶች በስልጠና ወቅት የሚያመጧቸውን የቴክኖሎጂ ሀሳቦችና የምርምር ውጤቶች ወደ ተግባራዊ ቢዝነስ እንዲቀይሩ፣የራሳቸውን ኢንተርፕራይዝ እንዲመሰርቱና ለሌሎችም የስራ እድል እንዲፈጥሩ የሚያስችል ነው ብለዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ የስማርት ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ግንባታ አስጀመሩ
Jul 24, 2026 172
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዛሬው ዕለት ከሰዎች ለሰዎች ድርጅት ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነውን የስማርት ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ግንባታ አስጀምረዋል። የስማርት ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ግንባታው ሲጠናቀቅ ወጣቶችን በማኑፋክቸሪንግ፣ በአውቶሞቲቭ፣ በኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክስ፣ በኮሙዩኒኬሽንስ፣ በቴክስታይል እና የሲኤንሲ (CNC) ቴክኖሎጂዎች ላይ ተግባር ላይ ያተኮረ እና ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም ሥልጠና እንደሚሰጥ ከንቲባዋ ገልጸዋል። ሀገርን ማልማት እና ከድህነት መላቀቅ በንድፈ ሐሳብ ብቻ በተገደቡ ትምህርቶች ማሳካት ስለማይቻል፣ ሐሳብን የሚያፈልቁ አዕምሮዎችን እና የሚሠሩ እጆችን ያጣመረ ክህሎት መር የሰው ኃይል እጅግ አስፈላጊ መሆናቸውን ከንቲባ አዳነች በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት አመልክተዋል። ዛሬ ያስጀመርነው ፕሮጀክት በቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ወጣቶቻችንን ከሥራ ፈላጊነት ወደ ሥራ ፈጣሪነት፣ ከንድፈ ሐሳብ ወደ ተግባር የሚያሸጋግር፣ አዲስ የሥራ እድል የሚፈጥር የክህሎት ድልድይ የሚሆን ነው ብለዋል። የዚህ ኮሌጅ ግንባታ በጥራትና በተቀመጠለት ጊዜ ተጠናቅቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ በልዩ ትኩረት የምንከታተለው ይሆናልም ነው ያሉት። ፕሮጀክቱን በትብብር የሚገነባው የረጅም ጊዜ የልማት አጋር የሆነው ሰዎች ለሰዎች ድርጅት እና የሚሠራው ለትውልድ የሚሻገር ዐሻራ ነው በማለት መሬታቸውን ለፕሮጀክቱ የለቀቁ አርሶ አደሮችንም አመስግነዋል።
የኢ.ፌ.ዲ.ሪ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በመጪዎቹ ሶስት ዓመታት የላቀ አገልግሎት ለመስጠት የቴክኖሎጂና ዲጂታል መሰረተ ልማት ይገነባል
Jul 24, 2026 222
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በመጪዎቹ ሶስት ዓመታት ተቋማዊ አቅምና ዝግጁነትን ለማሳደግ፣ ዜጋ ተኮር የላቀ አገልግሎት ለመስጠት የቴክኖሎጂና ዲጂታል መሰረተ ልማት ለመገንባት ይበልጥ ትኩረት አድርጎ እንደሚሰራ አስታወቀ፡፡ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በቀጣዮቹ ሶስት ዓመታት የመንግስት አገልግሎቶችን በዲጂታል ቴክኖሎጂ የተደገፈ፣ ተደራሽ፣ ቀልጣፋና ዜጋ-ተኮር ማድረግ የሚያስችል የሦስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድና ፍኖተ ካርታ ይፋ አድርጓል፡፡ ፍኖተ ካርታው የ«ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030» ስትራቴጂን መነሻ በማድረግ፣ የዜጎችን የአገልግሎት ተደራሽነት፣ ጥራትና ቅልጥፍና ማሳደግ የሚያስችሉ ቁልፍ የለውጥ አቅጣጫዎችን አካቷል። የኢ.ፌ.ዲ.ሪ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዮናስ አለማየሁ በመድረኩ እንደገለጹት፤ ፍኖተ ካርታው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በቀጣይ ሶስት ዓመታት ምን ዓይነት የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት መገንባት እንዳለበት በግልጽ የሚያመላክት ሰነድ ነው። የስትራቴጂክ ዕቅዱ መሠረትም መሶብ ባለፈው አንድ ዓመት ያከናወናቸውን ሥራዎች በመገምገም፣ በቀጣይ የሚከናወኑ የዲጂታል ሽግግር፣ የአገልግሎት ጥራት ማሻሻያ እና ተቋማዊ አቅም ግንባታ ሥራዎችን የሚመራ ይሆናል ብለዋል። ዕቅዱ ከ«ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030» ራዕይ፣ ከሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም አቅጣጫዎች እና ከሀገራዊ የዲጂታል ልማት ግቦች ጋር ተጣጥሞ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። በአገልግሎቱ የእቅድና ፕሮግራም ዳይሬክተር ደሳለኝ ድንገታ ባቀረቡት ጽሁፍ፤ በመሶብ የተዘጋጀው ስትራቴጂያዊ ፍኖተ ካርታ በሶስት ዋና ዋና የትኩረት መስኮች ላይ ያተኮረ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዚህም የመጀመሪያው ተቋማዊ አቅምና ዝግጁነትን ማሳደግ መሆኑን ጠቅሰው የመሶብን የመፈጸም አቅም ማጎልበት፣ ዘመናዊ የአፈጻጸም አመራር ሥርዓት መዘርጋት እንዲሁም የሰው ኃይል ብቃትን ማሳደግና ውጤታማ የሥራ ባህል መገንባት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በሁለተኛ ደረጃም ዜጋ ተኮር የላቀ አገልግሎት መስጠት ሲሆን የመሶብ አገልግሎቶችን ተደራሽ፣ ፍትሃዊና ዲጂታል ማድረግ፣ የዲጂታል አገልግሎት አጠቃቀምን ማስፋፋት ብሎም የጥሪ ማዕከል አገልግሎትን ማጠናከርና የተገልጋዮችን እርካታ ማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥርዓቶችን መዘርጋት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ በሶሰተኛ ደረጃም የላቀ ቴክኖሎጂና ዲጂታል መሰረተ ልማት መገንባት መሆኑን ጠቅሰው የሳይበር ደህንነትን ማጠናከርና ዘመናዊ የዲጂታል አገልግሎት ሥርዓቶችን ማልማት ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡ የፍኖተ ካርታው ዝግጅት የተመሠረተው በሀገራዊ የ10 ዓመት የልማት ዕቅድ፣ በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ ማዕቀፍ፣ በመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ፖሊሲ እንዲሁም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ላይ መሆኑንም አክለዋል፡፡ ዛሬ ይፋ የተደረገው ፍኖተ ካርታ፤ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ሙሉ በሙሉ በቴክኖሎጂ የተደገፈ፣ ቀልጣፋና ዜጋ ተኮር የመንግስት አገልግሎት ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውም ተመላክቷል፡፡
የኢትዮ-ቴሌኮም ቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የመሪነት ሚና መወጣት የሚያስችል ነው
Jul 23, 2026 329
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 16/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮ-ቴሌኮም ቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የመሪነት ሚና መወጣት የሚያስችል መሆኑን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ። ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ የ2018 በጀት ዓመትና የቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ አፈፃፀም ላይ በሰጡት መግለጫ፤ ኢትዮ ቴሌኮም ባለፉት ሰባት ዓመታት ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በትጋት ሲሠራ መቆየቱን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት የተጀመረውና ለሦስት ዓመታት የሚተገበረው"ቀጣዩ አድማስ" ስትራቴጂ፣ ሁለንተናዊ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን ለማፋጠን ያለመ መሆኑን አስገንዝበዋል። ስትራቴጂው ተቋሙ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የድርሻውን እንዲወጣ ከማስቻሉም በላይ፣ለአፍሪካ አጀንዳ 2063 እና ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስኬት ጠንካራ መሠረት የሚጥል መሆኑን ገልጸዋል። በስትራቴጂው የአንድ ዓመት አፈፃፀምም በርካታ የኔትወርክ ማስፋፊያና የማዘመን ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። በዚህም 603 አዳዲስ የሞባይል ጣቢያዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቅሰው፣ ይህም አጠቃላይ የሞባይል ጣቢያዎችን ቁጥር ወደ 10 ሺህ 613 ከፍ ማድረጉን አስታውቀዋል። በተጨማሪም 195 የገጠር ሞባይል ጣቢያዎች መገንባታቸውን ገልጸው፣ በዚህም 117 ወረዳዎች የቴሌኮሙ አገልግሎት ተደራሽ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ይህም የአገልግሎት ተደራሽነትን በማስፋት ዲጂታል አካታችነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። በ2018 በጀት ዓመት የኔትወርክ ማሻሻያና ማስፋፊያ ሥራዎች በስፋት መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ 264 ተጨማሪ ከተሞች የአራተኛ ትውልድ (4ጂ) አገልግሎት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። በዚህም የ4ጂ ኔትወርክ ሽፋን ያላቸው ከተሞች ቁጥር ወደ 1 ሺህ 200 ከፍ ማለቱን ገልጸዋል። በተጨማሪም ሰባት አዳዲስ ከተሞች የአምስተኛ ትውልድ (5ጂ) አገልግሎት በማግኘታቸው፣ የ5ጂ ተጠቃሚ ከተሞች ቁጥር 33 መድረሱን አስታውቀዋል። ኢትዮ ቴሌኮም በ2018 በጀት ዓመት 215 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ገቢ በማስመዝገብ የዕቅዱን 99 ነጥብ 7 በመቶ ማሳካቱንም ገልጸዋል። ይህም ከ2017 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ33 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት ያሳየ መሆኑን ገልጸዋል። በቴክኖሎጂና በመሠረተ ልማት ማስፋፊያ ሥራዎች የተመዘገበውን ውጤት መሠረት በማድረግ፣የኢትዮ ቴሌኮም አጠቃላይ የደንበኞች ቁጥር 90 ነጥብ 1 ሚሊዮን መድረሱን ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ 475 አዳዲስና የተሻሻሉ ምርቶችና አገልግሎቶች ለደንበኞች ማቅረብ መቻሉንም ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የቴሌብር ተጠቃሚዎች ቁጥር 60 ነጥብ 5 ሚሊዮን መድረሱን አስታውቀዋል።
የአፍሪካን ዕድገት ለማሳለጥ በታማኝ መረጃና ማስረጃ ላይ የተመሰረተ የፖሊሲ ውሳኔ ማሳለፍ ያስፈልጋል
Jul 23, 2026 406
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካን ፈጣን ዕድገት ለማሳለጥ በታማኝ መረጃና ማስረጃ ላይ የተመሰረተ የፖሊሲ ውሳኔ ማሳለፍ እንደሚያስፈልግ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) ገለጹ። ለሁለት ቀናት የሚቆየው 14ኛው የአፍሪካ የፖሊሲ ጥናት ጉባኤ "ፖሊሲን በፈጠራ፣ አካታችና ግልጽ ማስረጃ ማጠናከር" በሚል መሪ ሐሳብ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። በአህጉራዊ ጉባኤው ምሁራን፣ ተመራማሪዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎችና የልማት አጋሮች እየተሳተፉ ይገኛሉ። ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ የአፍሪካ የቴክኖሎጂ ለውጥ፣ የአየር ንብረት ጫና፣ የሕዝብ ቁጥር ዕድገትና የኢኮኖሚ ተግዳሮትን ለመቋቋም ታማኝና ጥራት ባለው መረጃ ላይ የተመሠረቱ የፖሊሲ ውሳኔዎችን ይጠይቃሉ። ኢትዮጵያም በመረጃ የተደገፈ የፖሊሲ ውሳኔ አሰጣጥን ለማጠናከር ባለ ስምንት አምድ ብሔራዊ የስታትስቲክስ ልማት ፕሮግራም ይፋ በማድረግ ወደ ሥራ መግባቷን ገልጸዋል። የብሔራዊ ስታትስቲክስ ሥርዓትን በዘመናዊ የዲጂታል አሠራር በማሸጋገር የግብርናና የኢኮኖሚ ተቋማት ቆጠራ፣ የሕዝብና ጤና ዳሰሳ እንዲሁም የቤተሰብ ደህንነት ዳሰሳዎች መካሄዳቸውን ተናግረዋል። የጥናት ውጤቶችና መረጃዎችን ከመሰነድ ባሻገር ወደ የበጀት ውሳኔዎችና የመንግሥት ፕሮግራሞች ተግባራዊ እርምጃ ሊቀየሩ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። በተጨማሪም እንደ የሰው ሠራሽ ዕውቀትና የሳተላይት መረጃ ያሉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን ሲጠቀሙ የግል መረጃ ጥበቃን የሥነ-ምግባር መርሆችንና የሕዝብን እምነት መጠበቅ ወሳኝ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈቃዱ ፀጋ በበኩላቸው፣ ምርምርና ጥናት ከፖሊሲ ሂደት ተነጥሎ በሪፖርት ብቻ መቅረት የሌለበት ወሳኝ ጉዳይ ነው ብለዋል። ተመራማሪዎችና ፖሊሲ አውጪዎች በቅርበት በመሥራት የጥናት ውጤቶችን ወደ ተግባራዊ የፖሊሲ ውሳኔዎች እንዲለወጡም ግፊት ማድረግ እንደሚኖርባቸው ጠቁመዋል። የአፍሪካን የኢኮኖሚ ሽግግር፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የትምህርትና የቴክኖሎጂ ተግዳሮቶች ለመፍታት ዕውቀት፣ ፈጠራና ትብብር ወሳኝ መሆናቸውን ገልጸዋል። የአፍሪካ የተፅዕኖ ግምገማ ተመራማሪዎች ኔትወርክ ሊቀመንበር ፕሮፌሰር አሞስ ንጁጉና፤ ለአህጉሪቱ የልማት ውጤታማነት ተመራማሪዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ መንግሥታትና የልማት አጋሮች በትብብር መሥራት እንዳለባቸው ተናግረዋል። የጥናት ውጤቶች በጥናት መድረኮች ብቻ ሳይወሰኑ ወደ ውሳኔ ሰጪዎች በመድረስ ለሕዝብ ፖሊሲዎችና ለልማት ውሳኔዎች ቀጥተኛ ግብዓት ሊሆኑ እንደሚገባም አመልክተዋል።
አምቦ ዩኒቨርሲቲ የተሻሻሉ የእንስሳት መኖ የሳር ዝርያዎችን ለአርሶ አደሮች ተደራሽ እያደረገ ነው
Jul 23, 2026 236
አምቦ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ አምቦ ዩኒቨርሲቲ የተሻሻሉ የእንስሳት መኖ የሳር ዝርያዎችን በማባዛት ለአርሶ አደሮች ተደራሽ እያደረገ መሆኑን አስታወቀ፡፡ በአምቦ ዩኒቨርሲቲ ጉደር ማሞ መዘመር ካምፓስ የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር አማን ሪቂቱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ተግባሩ ጎን ለጎን በምርምር የተገኙ ዝርያቸው የተሻሻለ የእንስሳት መኖ የሳር ዝርያዎችን በማባዛት ለአርሶአደሩ ተደራሽ እያደረገ ነው ። ዩኒቨርሲቲው የሳር ዝርያዎቹን በቶኬ ኩታዬ ወረዳ ውስጥ ለሚገኙ የአካባቢው አርሶአደሮች ተደራሽ በማድረግ የእንስሳት እርባታና ማድለብ ስራውን እያገዘ መሆኑን ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲው በሶስት ሄክታር መሬት ላይ አስር አይነት የተሻሻለ የእንስሳት መኖ የሳር ዝርያዎችን እያባዛ ለአርሶአደሮች እያሰራጨ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በዩኒቨርሲቲው ጉደር ማሞ መዘመር ካምፓስ የከብቶች ጤና ባለሙያ ዶክተር ጫሉማ ነገራ ናቸው፡፡ የሳር ዝርያዎቹ በውስጣቸው ሀይል ሰጭ እና ገንቢ ንጥረ ነገሮችን የያዙና ለእንስሳት እድገትና ጤና እንዲሁም የወተትና የስጋ ምርትን ለማሳደግ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው መሆናቸውን ተናግረዋል ። የሳር ዝርያዎቹ በተጨማሪም ከአካባቢው አየር ጠባይ ጋር የተላመዱና ከእርጥብነት በተጨማሪ በድርቆሽነት ለመኖነት የሚያገለግሉ በመሆናቸው በከብት እርባታና ማድለብ ስራ የተሰማሩ አካላትን ውጤታማ የሚያደርጉ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው የሳር ዝርያዎቹን እስከአሁን 100 ለሚሆኑ የአካባቢው አርሶ አደሮች በማሰራጨት ልማቱ እንዲስፋፋ ማድረጉን ጠቁመው በቀጣይ ተደራሽነቱን ለማስፋት የበለጠ እንደሚሰራ አመላክተዋል። በምዕራብ ሸዋ ዞን የቶኬ ኩታዬ ወረዳ ነዋሪ አርሶአደር ተፈራ ትርፌ፤ ከዚህ ቀደም በተሰማሩበት የወተት ላሞች እርባታ የመኖ አቅርቦት እጥረት ይገጥማቸው እንደነበር አስታውሰዋል ። አሁን ላይ ከዩኒቨርሲቲው ያገኙትን የተሻሻለ የሳር ዝርያ በማልማትና በመጠቀም የመኖ እጥረትን ከመቅረፍ ባሻገር የወተት ምርታማነትን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። አሁን ላይ ከአንድ ላም በቀን በአማካይ 12 ሊትር ወተት በማግኘት ገቢያቸውን ማሳደጋቸውን ጠቁመው ከወተት ሽያጭ በሚያገኙት ገቢ መኖሪያ ቤት መገንባታቸውን እና ልጆቻቸውን እያስተማሩ መሆኑን ገልጸዋል።