ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
አኩቴክ ዲያግኖስቲክ የህክምና ቱሪዝም ማዕከልነት ግብ ለማሳካት ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር ነው
Sep 15, 2026 212
አዲስ አበባ፤ መስከረም 5/2019 (ኢዜአ)፦ አኩቴክ ዲያግኖስቲክ ሀገሪቱን የህክምና ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር መሆኑን የአኩቴክ ዲያግኖስቲክ ዋና ዳይሬክተር ሄኖክ ታደሰ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በቅርቡ የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሜዲካል ኮሌጅ የሥራ እንቅስቃሴ መመልከታቸው ይታወሳል።   በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ አኩቴክ (ACCU-TECH) ዲያግኖስቲክ ላቦራቶሪ የሀገሪቱን የጤና ዘርፍ ወደ ከፍተኛ ምዕራፍ የሚያሸጋግር እና ለዘርፉ ልዩ መለያ እና አቅም ነው። ዘመናዊው ላቦራቶሪ በአንድ ጊዜ በርካታ ናሙናዎችን በመቀበል ለተወሰነ ጊዜ ሳምፕሎችን በጥንቃቄ ማቆየት የሚያስችል አቅም እንዳለውም ተናግረዋል። የአኩቴክ ዲያግኖስቲክ ዋና ዳይሬክተር ሄኖክ ታደሰ ለኢዜአ እንዳሉት፣ ስያሜው "አኩ" ትክክለኛነትን እና "ቴክ" ቴክኖሎጂን የሚወክል ሲሆን፣ የሚጠቀማቸው ዘመኑን የዋጁ ቴክኖሎጂዎች የምርመራ ውጤቶች ጥራት እንዲኖራቸው ያስችላሉ። ይህ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ ላቦራቶሪ ወደ ውጭ ሀገር ተልከው ይሠሩ የነበሩ የላቦራቶሪ ምርመራዎችን በማስቀረት ረገድ ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወትም ገልጸዋል።   የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ሕክምና ኮሌጅ ከሪቲና ፋርማሲዩቲካል ጋር በመተባበር የተቋቋመው ላቦራቶሪ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ሙሉ በሙሉ አውቶሜትድ የሆነ ነው ብለዋል። ላቦራቶሪው በምርመራ ሂደቶች ላይ የሚታዩ የውጤት መዘግየቶችንና የውጭ ምንዛሬ ወጪዎችን ለማስቀረት ጉልህ ሚና እንዳለውም ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም እስከ 68 በመቶ የሚደርሱ ስህተቶች ሊከሰቱ እንደሚችሉ አንስተው፣ አሁን ያለው ሲስተም ይህንን ዲጂታላይዝ በማድረግ ስህተቱን ወደ ዜሮ እንደሚያወርደው አስረድተዋል። ላቦራቶሪው በርካታ ናሙናዎችን በአንድ ጊዜ የመመርመር ብቃት ያለው ከመሆኑ ባሻገር ናሙናዎችን በጥንቃቄ የሚያቆይ መሆኑንም ተናግረዋል። ማሽኖቹ ከሰው ሰራሽ አስተውሎት (አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ) ጋር የተገናኙ በመሆናቸው ሥራን በቀላሉና በፍጥነት እንዲያከናውኑ ማስቻሉን አንስተዋል። በቀጣይም አገልግሎቱን በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉ አካባቢዎች ተደራሽ ለማድረግ በድሮን ናሙና መሰብሰብ የሚያስችል ተግባር ለማከናወን እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ላብራቶሪው ሀገሪቱን የህክምና ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካትም ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ተናግረዋል።
የመደመር አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲ አፍሪካ የነገውን የቴክኖሎጂ ዘመን በባለቤትነት እንድትመራ ትልቅ ሚና ይጫወታል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 12, 2026 360
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ):- አፍሪካ የነገውን የቴክኖሎጂ ዘመን በባለቤትነት እንድትመራ የመደመር አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። 18ኛው የብሪክስ ጉባኤ ዛሬ በህንድ ኒው ዴልሂ መካሄድ ጀምሯል። በጉባኤው ላይ እየተሳተፉ የሚገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ንግግር አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በንግግራቸው ዓለም አቀፍ ቀውሶች የሚያስከትሉት ጉዳት በአንድ ዘርፍ ላይ ብቻ ሳይወሰኑ ተደራራቢ መስተጓጎል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል። ሀገራት ቀውሶች ከመከሰታቸው በፊት የመቋቋም አቅም ሊገነቡ እንደሚገባ ጠቅሰው፤ በዚህ ረገድም ኢትዮጵያ ፈተናን መቋቋም የሚያስችሉ ስርዓቶችን እየገነባች እንደምትገኝ ተናግረዋል። መንግስት በምግብ ዋስትና ላይ ባከናወነው ተግባር ኢትዮጵያ ከውጭ ከሚገባ ስንዴ ጥገኝነት ሙሉ በሙሉ ወጥታ ራሷን መቻሏን ጠቅሰዋል። በመሆኑም ሀገሪቱ ለታቀደው የብሪክስ የሰብል ልውውጥ ማዕቀፍ (BRICS Grain Exchange) እንደ አምራችም ሆነ አቅራቢ ሆና ለመሳተፍ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል። በጤናው ዘርፍም የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ትልቅ ትምህርት መስጠቱን ነው የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ የሚያጋጥሙ ቀውሶችን ለመቋቋም የሀገር ውስጥ የማምረት አቅሟን እያሳደገች እንደምትገኝ ገልጸው፤ የፋርማሲዩቲካልና የመድኃኒት ማምረቻዎችንም እያስፋፋች መሆኗን ጠቁመዋል። በቴክኖሎጂው ዘርፍ ዲጂታል መሠረተ ልማት፣ ዲጂታል መታወቂያ (Digital ID)፣ የክፍያ ሥርዓቶች እና የመረጃ ልውውጥ በስፋት እየተገነቡ መሆናቸውን አንስተዋል። መረጃዎች ደህንነታቸው በተጠበቀ መልኩ በሕግ አግባብ ጥቅም ላይ እንዲውሉ እየተደረገ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ ሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) ይህንን ለውጥ የበለጠ እንደሚያጠናክረው አመልክተዋል። በቀጣዩ ትውልድ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ይበልጥ ሰዎችን ማገልገል፣ ብዙ ቋንቋዎችን መረዳት እና ሰፊ የሰው ልጅ እውቀት ማካተት እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል። አፍሪካ የነገውን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘመን በባለቤትነት ለመምራት የምርምር፣ የኮምፒውቲንግ አቅም፣ ክህሎት እና ተቋማት እንደሚያስፈልጋት አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ እየገነባች ያለችውም የመደመር አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲም አፍሪካ የወጠነችውን ግብ የማሳካት አላማ እንዳለው አመልክተዋል። ኢትዮጵያ አፍሪካን የሚወክል የቴክኖሎጂ አቅም ለመገንባት ከብሪክስ ተቋማት ጋር በጋራ ለመስራት ፍላጎት እንዳላትም ገልጸዋል። በተጨማሪም ሰዎችን ማዕከል ያደረገ የኤአይ አስተዳደር መደገፍ እንዳለበት እና ጥሩ አስተዳደር ከብቃት ጋር ሊጣጣም እንደሚገባ አሳስበዋል።
የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር የዲጂታል ግብር ክፍያ ሥርዓት ጀመረ
Sep 12, 2026 219
ሰመራ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ)፦የአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር የዲጂታል ግብር ክፍያ ሥርዓት ጀመረ። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የሰመራ ሎጊያ ከተማ ከንቲባ ኢንጂነር አህመድ ኑርሳሊም፤ የዲጂታል የግብር ክፍያ ሥርዓት ቀልጣፋ አሰራርን ከመዘርጋት ባለፈ ብልሹ አሰራርን ለመከላከል የሚያስችል ዘመናዊ አሰራር መሆኑን ገልጸዋል።   የግብር አሰባሰብ ሂደቱ ለብልሹ አሰራር እንዳይጋለጥ እና የግብር መሰወር ችግሮችን ለመከላከል የሚያስችል ስለመሆኑም ጠቅሰዋል። በመሆኑም ግብር ከፋዮች ምንም አይነት እንግልት ሳይገጥማቸው ባሉበት ሆነው የሚከፍሉበት ስርአት መዘርጋቱ አስደሳች መሆኑን ተናግረዋል። ግብር ከፋዮች በኢትዮጵያ ንግድ ባንክና በቴሌብር አማራጮች ባሉበት ሆነው ግብራቸውን በመክፈል ከእንግልት በጸዳ መልኩ ሃላፊነታቸውን በቀላሉ መወጣት ያስችላቸዋል ብለዋል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የአፋር ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የመሬት ቢሮ ኀላፊ ኡመር ኑር እና ሌሎችም የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል።
የመንግስታዊ አገልግሎቶችን በማዘመን የህዝብን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል 
Sep 10, 2026 356
ድሬዳዋ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የመንግስታዊ አገልግሎቶችን በማዘመን የህዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ተጠቃሚነት በላቀ ደረጃ ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ገለጹ። ጳጉሜን 5 "የነገ ቀን" በሚል ስያሜ በድሬዳዋ አስተዳደር በፈጠራና በቴክኖሎጂ ዘርፍ የተመዘገቡ እምርታዎችን የሚያመላክት የፓናል ውይይትና በአውደ ርዕይ ተካሂዷል።   ከንቲባ ከድር ጁሃር በወቅቱ እንደተናገሩት፣ የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን ተደራሽ በማድረግ የነገዋን ታላቅ አገር የመገንባቱ ጉዞ በተጨባጭ ውጤቶች እውን እየሆነ ነው። የተሻለች እና የበለፀገች አገር ለትውልድ ለማስረከብ በየደረጃው የሚደረገው ርብርብ ተጠናክሮ መቀጠሉንም ከንቲባው ተናግረዋል። በተለይ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎትን የጨበጠ የሲቪል ሰርቪስ ሠራተኛ በመገንባት ፈጣንና ቀልጣፋ የመንግስት አገልግሎቶችን ተደራሽ በማድረግ የነዋሪውን የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ እየተመለሰ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፈው አንድ ዓመት በከተማ አስተዳደሩ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እየተሰጡባቸው ባሉ አከባቢዎች አዎንታዊ ለውጦች እየተመዘገቡ መሆናቸውን ለአብነት አንስተዋል። በአስተዳደሩ ዲጂታል የአሰራር ሥርዓትን በላቀ ደረጃ ለማሳደግ በቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች፣ በድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ እና በግል ተቋማት የተጀመሩ የፈጠራና የቴክኖሎጂ የምርምር ሥራዎች የነገዋን ታላቅ አገር ለመገንባት መደላድል እየፈጠሩ ይገኛሉ ብለዋል።   በድሬዳዋ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ዘመናዊ፣ ቀልጣፋና ከሙስና የፀዳ አገልግሎት በመስጠት የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ የተጀመሩ ስራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። የነገ ቀን በድሬዳዋ ሲከበር ከመድረክ በተጨማሪ በአረጋዊያን መጦሪያ ማዕከል ለሚገኙ አቅመ ደካሞች ከንቲባው ማዕድ ያጋሩ ሲሆን የድሬዳዋ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራርም ተጎብኝቷል።   በስነስርዓቱ ላይ የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት አፈጉባኤ አብዲ ሙክታር፣ በብልጽግና ፓርቲ ድሬዳዋ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ፣ የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ፣ የአስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች፣ የኃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች እንዲሁም ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ አገልግሎት አሰጣጥና የሥራ ዕድል እያሰፋ ነው
Sep 10, 2026 246
ጅግጅጋ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ) ፦ዲጂታል ኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ አገልግሎት አሰጣጥን እያቀላጠፈና የሥራ እድልን እያሰፋ መሆኑን የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኢብራሂም ኡስማን ገለጹ። የጳጉሜን 5 "የነገ ቀን" በሚል ስያሜ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች እየተከበረ ሲሆን በሶማሌ ክልል ደረጃም ቀኑ በጂግጂጋ ከተማ በተለያዩ ዲጂታል የንቅናቄ መርሃ-ግብሮች ተከብሯል። በመርሃ-ግብሩ ላይ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኢብራሂም እንደገለጹት፤ በክልሉ በቴክኖሎጂና በሰው ኃይል ልማት ላይ በስፋት በመስራት ሁለንተናዊ እድገትን በዘላቂነት ለማስመዝገብ እየተሰራ ነው። በተለይ ዲጂታል አገልግሎትን በማስፋፋት ለአገልግሎት አሠጣጥ፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለክልሉ የኢኮኖሚ አቅም መጠናከር ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ አበረታች ውጤቶች ተገኝቷል ብለዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያን ማረጋገጥ በቴክኖሎጂ፣ በፋይናንስ፣ በትራንስፖርትና በሌሎችም ዘርፎች አሰራርን በማዘመን ለቀጣይ ትውልድ የተሻለች ሀገር ለማስረከብ ከፍተኛ ድርሻ እንዳለውም አስረድተዋል።   ለዚህም ስኬት የተቋማት የማስፈጸም አቅምን መገንባት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው፣ በክልሉ ተቋማትን በቴክኖሎጂ አቅርቦትና በሰው ኃይል የማደራጀት ሥራው ትኩረት እንደተሰጠው ገልጸዋል። ለአብነትም በክልሉ የመንግሥት አገልግሎቶችን ለማቀላጠፍ 13 መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎች መገንባታቸውን ጠቁመዋል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት መንግሥት ለዲጂታል መሠረተ ልማት ግንባታ ዘርፍ የሠጠው ልዩ ትኩረት የነገን የሀገሪቱን አድገት ለማፋጠን የሚያግዝ ነው። በዲጂታል ዘርፍ የኢትዮ ኮደርስ፣ የስታርትአፕ እና የዲጂታል ክህሎት ንቅናቄዎች የዜጎችን አቅም በመገንባት ረገድ ምቹ ሁኔታ እየፈጠሩ ይገኛሉ ሲሉም ገልጸዋል የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ መሀመድ አሊ በበኩላቸው እንዳሉት ፤ በክልሉ የዲጂታልና የፈጠራ ክህሎትን ለማዳበር ዘርፈ ብዙ ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ።   በተለይም በክልሉ በስፋት እየተሰጠ ያለው የ“ኢትዮ ኮደርስ” ሥልጠና የወጣቶችን ቴክኖሎጂ የመጠቀም አቅም በከፍተኛ ደረጃ እያሳደገው መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ቴክኖሎጂን ጥቅም ላይ በማዋል የመንግሥትን አገልግሎቶች ለማዘመን ፣ የስራ ዕድል ለመፍጠርና የሀገርን ልማት በማፋጠን በኩል ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው አስገንዝበዋል።   በጅግጅጋ ከተማ በተካሄደው በዚህ መርሃ - ግብር ላይ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ ባለድርሻ አካላት፣ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች፣ ወጣቶችና የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ተገኝተዋል።
የቴክኖሎጂ ልማትና ተጠቃሚነትን የማጠናከር ጉዳይ የነገ መዳረሻን ለመወሰን የሚያስችል ቁልፍ ተግባር ነው
Sep 10, 2026 142
ባህርዳር ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የቴክኖሎጂ ልማትና ተጠቃሚነትን የማጠናከር ጉዳይ የነገ መዳረሻን ለመወሰን የሚያስችል ቁልፍ ተግባር መሆኑን የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። ጳጉሜን 5 (የነገ ቀን) የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደን ጨምሮ ሌሎችም ከፍተኛ አመራሮችና ባለሙያዎች በተገኙበት ተከብሯል።   በመርሃ ግብሩ ላይ ንግግር ያደረጉት ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፤ የቴክኖሎጂ ልማትና ተጠቃሚነትን የማጠናከር ጉዳይ የነገ መዳረሻን ለመወሰን የሚያስችል ቁልፍ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። የዛሬ ችግሮቻችን በጋራ በመፍታት የነገውን መዳረሻችንን የምንተልምበት ጊዜው አሁን ነው ያሉት ርእሰ መስተዳድሩ በተለይም ቴክኖሎጂን መፍጠር፣ በመቅዳትና በስፋት መጠቀም ይገባናል ብለዋል። በተጨማሪም ማህበረሰባዊ ካፒታልን፣ ገንዘብን፣ የአካባቢ ጸጋን በማልማት ጥቅም ላይ የማዋል ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ሲሉ ተናግረዋል።   የክልሉ ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ባንችዓምላክ ገብረማርያም፤ የዲጂታል ሲቪል ሰርቪስ ግንባታን ዕውን በማድረግ ነገን የተሻለ ለማድረግ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራዎች ውስጥ አንዱ የሆኑው የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ለዚህ ጥሩ ማሳያ መሆኑን አንስተው ይበልጥ የማስፋትና ተደራሽነቱን የማብዛት ስራ ይሰራል ብለዋል።
በአፋር ክልል ዲጂታል አገልግሎትን የማስፋፋት ቅንጅታዊ ተግባራት ይጠናከራሉ
Sep 10, 2026 409
ሰመራ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ዲጂታል አገልግሎትን በማስፋፋት የህዝብ እርካታ ለማሳደግ የተጀመሩ ቅንጅታዊ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአፋር ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የመሬት ቢሮ ኀላፊ አቶ ኡመር ኑር ተናገሩ። የጳጉሜን 5 "የነገው ቀን" በአፋር ክልል ሠመራ ከተማ "ለተቀናጀ አገልግሎት ወደ ዲጂታል መንግሥት" በሚል መሪ ቃል፣ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በተለያዩ መርሃ ግብሮች ድምቀት ተከብሯል።   በዕለቱ የተገኙት የአፋር ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የመሬት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡመር ኑር እንዳሉት፤ "የነገ ቀን" ሲከበር በዲጂታል አሰራር የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን በማቀላጠፍ የህዝብ እርካታን ለማሳደግ ቁርጠኝነትን በማሳየት መሆን አለበት። በክልሉ የተቀናጀ የዲጂታል አገልግሎትን በመተግበር የመንግሥት አገልግሎት ጥራትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ልዩ ትኩረት መሰጠቱን አመልክተዋል። በተደመረ አቅምና በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ የሥራ ዕድል ፈጠራና ሀገራዊ ዕድገትን ለማፋጠን በአብሮነትና በቁርጠኝነት መንቀሳቀስ ወሳኝ መሆኑንም በአፅንኦት ገልጸዋል።   ዲጂታል አገልግሎትን በማስፋፋት የህዝብ እርካታን ለማሳደግ የተጀመሩ ቅንጅታዊ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸው፣ በዚህም የነገን ቀን የተሻለ ለማድረግ ይሰራል ብለዋል። የክልሉ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መሐመድ አህመድ በበኩላቸው፤ በክልሉ በዲጂታል የታገዘ የመንግስት አገልግሎት በስፋት እየተተገበረ መሆኑን ገልጸው፣ ይህም የበለጸገችና ጠንካራ ሀገርን ለመገንባት ተጨማሪ አቅም ይፈጥራል ብለዋል።   በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በማስፋፋት ቀልጣፋና ዘመናዊ አሠራር መዘርጋት መቻሉን ጠቁመዋል። በዲጂታል የታገዘ ዘመናዊ አሰራር መተግበሩ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚታዩ ህገ-ወጥና የተዝረከረኩ አሠራሮችን ሙሉ በሙሉ ለማስቀረት ከፍተኛ አቅም ፈጥሯል ብለዋል። በክልል ደረጃ የሚሰጡ ማናቸውም አገልግሎቶች በቴክኖሎጂ መታገዛቸው ውጤታማ ተግባራት ለማከናወን እያስቻለ መሆናቸውን ጠቁመዋል። የ"ነገው ቀን" አከባበር መርሃ ግብር ላይ የሴክተር መሥሪያ ቤቶች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የቴክኖሎጂ ባለሙያዎችና የመንግሥት ሠራተኞች ተገኝተዋል።
የዲጂታላይዜሽን ጉዞው በከተማው የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን የሚያሳልጥ ነው
Sep 10, 2026 93
ወልድያ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የዲጂታላይዜሽን ጉዞው በከተማው የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን እያሳለጠ መሆኑን የወልድያ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ገለጹ። በወልድያ ከተማ የ‘ነገ’ ቀንን ምክንያት በማድረግ የፓናል ውይይት ተካሂዷል።   የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ አቶ ንጉስ ዝናቡ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ እየተተገበረ የሚገኘው የዲጂታላይዜሽን አሰራር የከተማዋን እድገትና የህዝቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ይገኛል። በከተማው እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች ተስፋ ሰጪና ህብረተሰቡን ተጠቃሚ እያደረጉ መሆናቸውንም ገልጸዋል። በተለይም የኮሪደር ልማት፣ የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትና ሌሎች የዲጂታላይዜሽን አሰራሮችን በማስፈን የህዝቡን እርካታ ማሳደግ መቻሉን አስረድተዋል። በመሆኑም በአዲሱ ዓመት አመራሩና ባለሙያው የቴክኖሎጂ አሰራርን ፈጥኖ በመላመድ፣ እውቀትና ክህሎትን በመጨበጥ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት ራሱን ማዘጋጀት እንዳለበት አሳስበዋል። የዲጂታላይዜሽን ንቅናቄው የወደፊቷን የወልድያ እድገት በፅኑ መሰረት ላይ ለመገንባትና የህዝቡን እርካታ ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑንም አስገንዝበዋል። የከተማ አስተዳደሩ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ኢትዮጵስ አያሌው ፤ በከተማዋ የተጀመሩት የስማርት ሲቲና የዲጂታል አሰራሮች በህብረተሰቡ ዘንድ የሚነሱ የመልካም አስተዳደርና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን እየፈቱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የመሬት፣ የንግድ፣ የኮንስትራክሽንና የከተማ ፕላን መረጃዎችን ወደ ዲጂታል ሲስተም በማስገባት ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው አሰራርን ለማስፈን የተደረገው ጥረት አበረታች መሆኑንም አፈ ጉባኤው ተናግረዋል። የከተማ አስተዳደሩን አሰራሮች ወደ ዲጂታል ስርዓት የመቀየር ስራ ተጨባጭ ውጤት እያመጣ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ጽህፈት ቤት የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ቡድን መሪ አቶ ብርሃኑ እንዳውቄ ናቸው።   ለዚህም በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከ11 በላይ ሲስተሞችን በመዘርጋት ከ82 በላይ የአገልግሎት አይነቶችን ለተገልጋዩ ማህበረሰብ መስጠት መቻሉን ገልጸዋል። በዚህም ከሁለት ሺህ በላይ ለሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች ፈጣን፣ ፍትሃዊና ከብልሹ አሰራር የጸዳ አገልግሎት መስጠት መቻሉን አስረድተዋል። በተጨማሪም በከተማዋ የሲሲቲቪ (CCTV) ካሜራ፣ የስማርት ስክሪንና የስማርት ትራንስፖርት ትግበራ መጀመሩን ነው የተናገሩት። በወልድያ ከተማ በተካሄደው የፓናል ውይይት ላይ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች፣ ባለሙያዎችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳታፊ ሆነዋል።
በክልሉ ዜጎችን በዲጂታል ክህሎት በማብቃት የሥራ ዕድልና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የተጀመሩ ተግባራት ይጠናከራሉ
Sep 10, 2026 146
ሆሳዕና፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ዜጎችን በዲጂታል ክህሎት በማብቃት የሥራ ዕድልና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አንተነህ ፈቃዱ ገለጹ። በክልሉ "የነገ ቀን" የዲጂታል ልህቀት ለኢትዮጵያ ማንሰራራት! በሚል መሪ ሀሳብ በክልል ደረጃ በሆሳዕና ከተማ ተከብሯል።   የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ሀላፊ አቶ አንተነህ ፈቃዱ በዚሁ ወቅት እንዳሉት በክልሉ የዜጎችን ዲጂታል ክህሎት በማሳደግ የተወዳዳሪነት አድማስን ለማስፋት የተጀመሩ ተግባራት ይጠናከራሉ። በተለይ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከ310 ሺህ 800 በላይ ዜጎች የተሳተፉ ሲሆን ስልጠናቸውን ያጠናቀቁ ከ237 ሺህ በላይ ሰልጣኞችም እውቅናና ምስክር ወረቀት አግኝተዋል ብለዋል። ስልጠናው በዲጂታል ቴክኖሎጂ ብቁ የሆኑና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ሥራ ፈጣሪ ዜጎችን ለማፍራት አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። አቶ አንተነህ እንደገለጹት በክልሉ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን 7 መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎች ተገንብተው ለአገልግሎት በመብቃታቸው የተገልጋይን እንግልት ማስቀረት ተችሏል ብለዋል።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ልዩ አማካሪ ንጉሴ አስረስ (ዶ/ር) በበኩላቸው በክልሉ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አሰራርን በመተግበር የአገልግሎት ጥራትና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ ሲሰራ ቆይቷል ብለዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በቴክኖሎጂ የበቃ ትውልድን የመገንባት ስራ አይነተኛ ሚና አለው ነው ያሉት፡፡ የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት አብድልሙህሲን ሀሰን (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት የበለፀገች ሀገርን ለተተኪው ትውልድ ለማስተላለፍ በዲጂታል ቴክኖሎጂ የሰለጠነ የሰው ሀይል ግንባታ ላይ አተኩሮ መስራት ያስፈልጋል።   ለክልሉ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ሽግግር ስኬታማነት ዩኒቨርሲቲው የሚጠበቅበትን ድጋፍ እያበረከተ መሆኑንም ተናግረዋል። በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ባገኘው እውቀት በቴክኖሎጂ የታገዘ የፈጠራ ሥራዎችን በማከናወን ተጠቃሚ መሆን እንደጀመረ የተናገረው ደግሞ በመድረኩ የተገኘው ወጣት ሙአዝ በድሩ ነው። የነገ ቀንን በማስመልከት በተዘጋጀ የውይይት መድረክ የክልሉ፤ የዞንና የተለያዩ መዋቅሮች ከፍተኛ አመራሮች፣ ተማሪዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተሳትፈዋል።
የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት ዲጂታል አሰራርን ማስፋፋት ዘመኑ የሚጠይቀው ጉዳይ ነው
Sep 10, 2026 96
ሚዛን አማን፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የቴክኖሎጂ ሽግግርንና ዲጂታል አሰራርን ማስፋት የጊዜው ወሳኝ እርምጃ መሆኑ ተመላከተ። ጳጉሜን 5 "የነገ ቀን" በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በክልል ደረጃ በሚዛን አማን ከተማ በፓናል ውይይት ተከብሯል።   በመድረኩ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አልማው ዘውዴ፤ ነገን ለሚዋጀው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ሥርዓት ባለፉት ዓመታት በዘርፉ የተከናወኑ ተግባራት ጠንካራ መሠረት የጣሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ቴክኖሎጂን መሠረት ያደረጉ ተግባራትን ማስፋፋት የጊዜው ወሳኝ ፍላጎት መሆኑን ተረድቶ ሁሉም ዜጋ ለዚህ አስፈላጊውን ዝግጅት ሊያደርግ እንደሚገባም አሳስበዋል። በክልሉም በሁሉም የልማት መስኮች አሠራሮችን በማዘመን ፈጣን ዕድገትና ለውጥ ለማስመዝገብ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የክልሉ ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ቢሮ ኃላፊ ረዳት ፕሮፌሰር ዘመድኩን ሰሎሞን በበኩላቸው፤ ባለፉት ዓመታት የተመዘገቡ ስኬቶች ሀገራዊውን የ"ዲጂታል 2030" ራዕይ እውን ለማድረግ የሚያስችሉ ጠንካራ መሠረቶችን የጣሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በክልሉ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስደው ወደ ቴክኖሎጂ ፈጠራ ሥራዎች የገቡ ወጣቶች እየተፈጠሩ መምጣታቸውን የጠቆሙት ኃላፊው፤ እስካሁንም ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን በላይ የክልሉ ነዋሪዎች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት መሆናቸውን ገልጸዋል። በክልሉ በተደራጁ የመሶብ የአንድ ማዕከላት በኩል ከ50 በላይ አገልግሎቶች በዲጂታል መንገድ እየተሰጡ እንደሚገኝ የጠቆሙት ኃላፊው፤ በዚህም ዜጎች በቤታቸው ሆነው ወይም ማዕከላት ድረስ በመሄድ ፈጣን አገልግሎት ማግኘት መጀመራቸውን አክለዋል። የውይይት ተሳታፊ የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን በበኩላቸው፤ በዞኑ ደረጃ የአገልግሎት አሰጣጥ ሂደቱን ሙሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል ሥርዓት ለማሸጋገር ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።   በሚዛን አማን ከተማ የጀመሩት ሁለት የዲጂታል ማዕከላት ውጤታማ አገልግሎት መስጠት መቻላቸውን የጠቆሙት አቶ ሀብታሙ፤ ይህንን አሰራር ወደ ሌሎች የዞኑ ከተሞች ሙሉ በሙሉ ለማስፋት አስፈላጊው ዝግጅት መጠናቀቁንም አስረድተዋል። በሚዛን አማን ከተማ በተካሄደው የጳጉሜን 5 "የነገ ቀን" የፓናል ውይይት መድረክ ላይ የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በርካታ የመንግሥት ሠራተኞች ተገኝተዋል።
በክልሉ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂን ስኬታማ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ - ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ
Sep 10, 2026 90
ጋምቤላ ፤ጳጉሜ 5/2018 (ኢዜአ)፡- በክልሉ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂን ስኬታማ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። ጳጉሜ 5 የነገ ቀን ’’የዲጂታል አብዮት ለነገዋ ኢትዮጵያ’’ በሚል መሪ ሃሳብ በጋምቤላ ከተማ በፓናል ውይይት ተከብሯል።   ርዕሰ መስተዳድሯ ዕለቱን አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክት የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂን ስኬታማ ለማድረግ የተጀመሩት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። በመደመር እሳቤ ባለፉት ዓመታት በቴክኖሎጂ ዘርፍ በተከናወኑ ተግባራት እንደ ክልልም ሆነ እንደ ሀገር በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል። የዲጂታል ኢኮኖሚውን ስኬታማ ለማድረግ በኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና እና በሌሎችም የክልሉን ወጣቶች በማሳተፍ የዲጂታል ቴክኖሎጂውን ዘርፍ ለማስፋት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በተለይም የክልሉ ወጣቶች የቴክኖሎጂ ክህሎታቸውን በማዳበር በዲጂታል ኢኮኖሚው ግንባታ የበኩላቸውን ሚና ለመወጣት ጠንክረው ሊሰሩ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን፣ የሳይበር ደህንነትንና የዳታ አስተዳደርን በማጠናከር ለዜጎች ቀልጣፋና የዘመነ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የዕለቱ በዓልም በለውጡ ዓመታት የተመዘገቡትንና ለኢትዮጵያ ማንሰራራት መሰረት የጣሉ ስኬቶችን ለማብሰርና ለማጠናከር ያለመ መሆኑን ርዕሰ መስተዳድሯ ገልጸዋል።   የክልሉ ስራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊና የበዓሉ አስተባባሪ ኢንጂነር ጓነር ጆክ በዚሁ ጊዜ የነገ ቀንን ስናከብር በአዲስ ተስፋና ተነሳሽነት ሰው ተኮር አገልግሎቶችን ለማጠናከር መሆኑን ተናግረዋል። በክብረ በዓሉ ላይ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና የከተማው ነዋሪዎች የተገኙ ሲሆን በመርሃ ግብሩ ላይ ዕለቱን በማስመልከት የመነሻ ጽሁፍ ቀርቦ በተሳታፊዎች ውይይት ተደርጎበታል።
የመሶብ አንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት የዜጎችን የአገልግሎት እርካታ ያሳደገ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ያስቻለ ነው
Sep 10, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የመሶብ አንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት የዜጎችን የአገልግሎት እርካታ ያሳደገ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ያስቻለ መሆኑን የአዲስ አበባ ፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ቢሮ ገለጸ። የአገልግሎቱን ተደራሽነት ይበልጥ ለማስፋፋት እየተሠራ መሆኑም ተጠቁሟል።   የጳጉሜን 5 "የነገ ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት የተዘጋጀና የማዕከሉን የአንድ ዓመት ጉዞ የሚያስቀኝ የፓናል ውይይት "ከአገልግሎት ስብራት ወደ ዲጂታል ብስራት" በሚል መሪ ሐሳብ እየተካሄደ ይገኛል። በውይይቱ ላይ የአዲስ አበባ ፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ቢሮ በቢሮ ኃላፊ ደረጃ የአገልግሎት አሰጣጥና አውትሶርስ ዘርፍ ኃላፊ አቶ በቀለ ተመስገን እንደተናገሩት፤ ከዚህ ቀደም የነበረው የአገልግሎት አሰጣጥ ዜጎችን ለእንግልት የሚዳርግና የግልጽነት ችግር የነበረበት ነው፡፡ ከ100 ዓመታት በላይ የተሻገረው የሀገራችን የሲቪል ሰርቪስ ሥርዓት የዜጎችን ፍላጎት ማሟላት በማያስችል የተወሳሰበ ቢሮክራሲ የተሳሰረና የአገልግሎት ስብራት የነበረበት በመሆኑ ለልማት ማነቆ ሆኖ መቆየቱን አስታውሰዋል። መንግሥት በዘርፉ ያካሄደው ሪፎርም በዘርፉ የነበሩ እንቅፋቶችን ከመሠረቱ የፈታ፣ የዲጂታል አገልግሎት አሰጣጥ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን የፈታ፣ የዜጎችን እርካታ ያሳደገ፣ እንዲሁም አሠራሩን ፈጣን፣ ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተጠያቂነት የሰፈነበት ያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። ዲጂታል ቴክኖሎጂ የህልውናና የዘመናዊነት መገለጫ መሆኑን የጠቆሙት ኃላፊው፤ የመሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል የመንግሥት አገልግሎት እስካሁን ለ700 ሺህ ያህል ዜጎች አገልግሎት መስጠት መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ዓለም አቀፍ መስፈርቶችን ያሟሉ 11 ማዕከላትና 1 ተንቀሳቃሽ የማዕከል አገልግሎት ለህብረተሰቡ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመው፤ በቀጣይም 3 ተጨማሪ ተንቀሳቃሽ አገልግሎት መስጫዎችና 20 ተጨማሪ የመሶብ ማዕከላት ተገንብተው ወደ ሥራ እንደሚገቡ አስታውቀዋል።          
የዲጂታል የመሬት መረጃ ሥርዓት የከተሞችን የመሬት አስተዳደር ያዘምናል
Sep 10, 2026 109
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ):- ሁለገብ የመሬት መረጃ ሥርዓት የከተሞችን የመሬት አስተዳደር ወደ ዲጂታል ሥርዓት በማሸጋገር ዘመናዊ፣ ዘላቂ፣ ቀልጣፋ እና ግልጽ የመሬት አገልግሎት ለመስጠት እንደሚያግዝ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ገለጸ። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር እና የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የመሬት አስተዳደር ሥርዓቱን ተግባራዊ ለማድረግና በዘርፉ በጋራ መሥራት በሚያስችላቸው ጉዳዮች ዙሪያ የትብብር ስምምነት በመፈራረም የጋራ መግለጫ ሰጥተዋል። በከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር የመሬትና ካዳስተር መሪ ሥራ አስፈጻሚ ብዙአለም አድማሱ እንደገለፁት፤ የተቋማቱ ትብብር የኢትዮጵያን የከተማ መሬት መረጃ ሥርዓት ለማዘመንና የመሬት አገልግሎቶችን ይበልጥ ቀልጣፋና ግልጽ ለማድረግ ያለመ ነው። ሥርዓቱ ሀገሪቱ ከሕጋዊ ካዳስተርና ከፊስካል ካዳስተር ወደ የተቀናጀ ሁለገብ ካዳስተር ሥርዓት የምታደርገውን ሽግግር የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል። የሕጋዊ ካዳስተር ሥርዓት የዜጎች፣ የመንግሥትና የባለሀብቶችን የመሬት ይዞታና ሕጋዊ ሰነዶች በግልጽ እንዲመዘገቡ በማድረግ የይዞታ ዋስትናንና የንብረት መብትን እንደሚያጠናክርም አመልክተዋል። የፊስካል ካዳስተር ደግሞ የመሬትና የንብረት ግምት መረጃዎችን ከካዳስተር ካርታ ጋር በማገናኘት ፍትሃዊና ትክክለኛ የንብረት ግብር ሥርዓት መዘርጋት ያስችላል ነው ያሉት። የትብብር ስምምነቱ የብሔራዊ የተቀናጀ የመሬት መረጃ ሥርዓትን ማልማትና ማዘመን፣ የንብረት ግብር ሥርዓትን ማሻሻልና በከተሞች በስፋት ተግባራዊ ማድረግን የሚያካትት መሆኑን ገልጸዋል። በፌዴራል፣ በክልልና በከተማ ተቋማት መካከል የመሬት መረጃ ልውውጥን ማቀላጠፍ፣ የመረጃ አስተዳደርና ተናባቢነትን ማጠናከር እንዲሁም የኢ-ላንድ አገልግሎትና ዲጂታል የሥራ ሂደቶችን ማስፋት የስምምነቱ አካል መሆናቸውን አስታውቀዋል። ሁለቱ ተቋማት የመሬትና የካዳስተር ሥርዓቶች፣ የንብረት ምዝገባና የንብረት ግብር ሥርዓቶች፣ የመረጃ ማዕከላትና የአይሲቲ መሠረተ ልማቶች ከሳይበር ጥቃት እንዲጠበቁም በመረጃ ደህንነት ዘርፍ በጋራ እንደሚሠሩ ገልጸዋል። የተቋማቱ ትብብር የመሬት አስተዳደርን በቴክኖሎጂ ለማዘመን፣ የመረጃ ደህንነትን ለማጠናከርና ለዜጎች የተሻለ የመሬት አገልግሎት ለማቅረብ የሚያግዝ ሲሆን፣ ከዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ጋርም የሚጣጣም መሆኑን ገልጸዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጂኦስፔሻልና ስማርት ፔይመንት ማዕከል ዳይሬክተር ቢንያም አበባው በበኩላቸው፣ የመሬት መረጃ ወሳኝ የመረጃ ሀብት በመሆኑ ከሳይበር ጥቃት ለመጠበቅ በጋራ መሥራቱ ትልቅ ጠቀሜታ አለው ብለዋል። አስተዳደሩ ባለፉት ዓመታት የመሬት ዲጂታላይዜሽንን የሚያግዙ ቴክኖሎጂዎችንና ፕሮጀክቶችን የማልማት ስራዎችን መሥራቱንና የዛሬው ስምምነት የተገኙ ልምዶችን በማሳደግ የሁለገብ ካዳስተር ሥርዓቱን ለተለያዩ ከተሞች ለማስፋት አቅም እንደሚፈጥር አስረድተዋል። በስምምነቱ የሀገራዊ የተቀናጀ የመሬት መረጃ ሥርዓት ልማትን ማዘመን፣ የንብረት ግብር ሥርዓት፣ የመረጃ አስተዳደር፣ የኢ-ላንድ አገልግሎት፣ የሳይበር ደህንነትና መሠረተ ልማት፣ ዘመናዊ ጂኦስፓሻል ቴክኖሎጂና የ3ዲ ካርታ ሥራዎች ላይ በጋራ እንደሚሰራ ገልፀዋል። ይህም የመሬት አስተዳደርን በዲጂታል ሥርዓት ለማዘመን ከሚደረገው ጥረት በተጨማሪ የመሬት መረጃ ደህንነትን በማጠናከር ቀልጣፋና አስተማማኝ የመሬት አገልግሎት ለመፍጠር እንደሚያግዝ ተመላክቷል።
ዲጂታል የመንግስት አገልግሎትን በማስፋፋት የኢትዮጵያን ነገ ብሩህ ለማድረግ መሰረት ተጥሏል- ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Sep 10, 2026 89
አርባ ምንጭ፣ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፡-ዲጂታል የመንግስት አገልግሎትን በማስፋፋት የኢትዮጵያን ነገ ብሩህ ለማድረግ መሰረት መጣሉን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ተናገሩ፡፡ ጳጉሜን-5 "የነገ ቀን" ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደን ጨምሮ የክልሉ፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር የሥራ ሃላፊዎች እና ባለሙያዎች በተገኙበት በክልል ደረጃ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተከበረ ይገኛል።   በመድረኩ ላይ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ እንዳሉት በክልሉ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋ የመንግስት አገልግሎት ለመስጠት ለዲጂታል አገልግሎት መስፋፋት ትኩረት ተሰጥቷል። ዲጂታል 2030 ስትራቴጂን ለማሳካት በሰው ሀይል ልማትና በተቋማት ግንባታ ላይ ይበልጥ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በተለይ ዲጂታል የመንግስት አገልግሎትን በማስፋፋት የኢትዮጵያን ነገ ብሩህ ለማድረግ መሰረት መጣሉን ገልጸዋል። ለአብነትም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ቀደም ሲል ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት ማስቻሉን ገልጸዋል። ነገን የተሻለ ለማድረግ ኢትዮጵያ ዛሬ በየዘርፉ እያስመዘገበቻቸው ያሉ ስኬቶች የማንሰራራት ጉዞዋን እንደሚያቀላጥፈውም አመልክተዋል። እንደ ሀገር የተጀመሩ ሜጋ ፕሮጀክቶችን እውን ለማድረግ የህብረተሰቡ ንቁ ተሳትፎ ቀጣይነት ባለው መልኩ መጠናከር እንዳለበትም አስገንዝበዋል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ሃላፊ ቦጋለ ቦሼ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት በክልሉ የዲጅታል አሠራር በመዘርጋቱ የዜጎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ለውጦች ተመዝግበዋል። የተጀመረው የብልጽግና ጉዞ እንዲሳካ የዲጂታል ዘርፉ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ያሉት ኃላፊው ዲጂታል 2030 ስትራቴጂን ለማሳካት በቅንጅት እንደሚሰራም አመልክተዋል። በመድረኩ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስኬቶችና የወደፊት አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ ፓናል ውይይት ተካሂዷል፡፡          
ሸገር ከተማ የህዝብ አገልግሎትን ለማዘመንና የነገ ከተማ ራዕይን ለማሳካት ዲጂታል ሽግግሯን እያፋጠነች ነው
Sep 10, 2026 139
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ):-ሸገር ከተማ የህዝብ አገልግሎቷን ለማዘመንና የነገ ከተማ ራዕይን ለማሳካት ዲጂታል ሽግግሯን እያፋጠነች መሆኑን ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) ገለጹ። የሸገር ከተማ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) ጳጉሜን 5 የነገ ቀንን ምክንያት በማድረግ በኤካ ጣፎ ክፍለ ከተማ የተገነባውን የመሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት ህንፃን አስመርቀው ሥራ አስጀምረዋል፡፡ ከንቲባው በዚሁ ወቅት እንዳሉት ፤ ሸገር ከተማ የነገ ከተማ ራዕይን ለማሳካት ቴክኖሎጂን፣ ዲጂታላይዜሽንንና ዘላቂ የከተማ ልማትን በትኩረት እየተገበረች ነው።   ቴክኖሎጂ የሥራ ቅልጥፍናን ከማሳደግ ባለፈ ከህዝብ ጋር ያለውን ግንኙነትና የአገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል ወሳኝ ሚና እንዳለውም ተናግረዋል። ከተማዋ ከተመሠረተች ጀምሮ የመሬት፣ የኢንቨስትመንትና የተለያዩ ዘርፎች መረጃዎችን ዲጂታል በማድረግ ላይ መሆኗን ከንቲባው ገልጸዋል። በተጨማሪም የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት በከተማዋና በአራት ክፍለ ከተሞች እየተሰጠ ሲሆን፣ ከ280 ሺህ በላይ ዜጎች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስታውቀዋል። በኤካ ጣፎ ክፍለ ከተማ የተመረቀው የመሶብ ዲጂታል አገልግሎት ህንፃ የከተማዋን ዲጂታል ሽግግር በማጠናከር የህዝብ አገልግሎቷን ይበልጥ ለማዘመን ያግዛል። ስለ ቴክኖሎጂ፣ ስለ ዲጂታላይዜሽንና ስለ ነገ ቀን ሳናስብ ምንም ዓይነት ውጤት መፍጠር አንችልም ሲሉም ከንቲባው አስገንዝበዋል።      
ብሔራዊ የፋይዳ መታወቂያ ከኢትዮጵያ ባሻገር በዛምቢያ፣ሞዛምቢክና ቡሩንዲ የሙከራ ትግበራ ሊጀምር ነው
Sep 10, 2026 174
አዲስአበባ፤ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ ብሔራዊ የፋይዳ መታወቂያ ከኢትዮጵያ ባሻገር በዛምቢያ፣ ሞዛምቢክ እና ቡሩንዲ የሙከራ ትግበራ ሊጀምር መሆኑን የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም (ፋይዳ ቨርስ) ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ዮዳሄ አርአያሥላሴ ገለጹ። በኢትዮጵያ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተመዝጋቢዎች ቁጥር 50 ሚሊዮን መድረሱንም ተናግረዋል። ዋና ሥራ አስፈጻሚው የነገ ቀንን አስመልክቶ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፥የፋይዳ መታወቂያ “አንድ ሰው አንድ ነው”በሚል መርህ የዲጂታል ማንነትን የመመዝገብና የማረጋገጥ ሥራን እያከናወነ ነው ብለዋል። ይህም ወንጀልን ለመከላከል፣አገልግሎቶችን በዲጂታል በማስተሳሰር ለማሳለጥና በግለሰቦች፣ በተቋማትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት መካከል አስተማማኝ ትስስርን ለመፍጠር የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ፋይዳን ከአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ጋር የማሰናሰል ሥራ ተሠርቶ እስካሁን 150 የመንግሥት፣ የግል፣ የስታርታፕ እና ሌሎች ተቋማት በፋይዳ ትስስር ማድረጋቸውን ተናግረዋል። በፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ከ200 ሚሊዮን በላይ ማንነትን የማረጋገጥ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የምዝገባ ማዕከላትን የማስፋፋት ሥራ ተሠርቶ የጣቢያዎቹ ቁጥር ወደ 12 ሺህ ገደማ መድረሳቸውን የጠቀሱት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፥ በዚህም እስካሁን 50 ሚሊዮን ሰዎች መመዝገባቸውን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም ወደ ሰፊ የዲጂታል መሠረተ ልማት ማዕከል በማደጉ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ሥር በልማት ድርጅትነት መቋቋሙን አስታውሰዋል። ፋይዳ ቨርስ ከፋይዳ መታወቂያ በተጨማሪ የፋይዳ ዲጂታል ቦርሳ፣ የዲጂታል አገልግሎቶች የንግድና ተቋማት መፍትሔዎችን በተሳለጠ መንገድ ለመስጠት እንደሚሠራ ጠቁመዋል። ብሔራዊ የፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት በዲጂታል ቴክኖሎጂ እና በማክሮ ኢኮኖሚው ዘርፍ ኢትዮጵያ እያመጣች ያለው አዎንታዊ ለውጥ በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ከፍተኛ ትኩረት ማግኘቱንም ነው ያስረዱት። ይህም በርካታ የአፍሪካ ሀገራት የኢትዮጵያን ተሞክሮዎች እንዲቀስሙና በትብብር ለመሥራት ከፍላጎት ያለፈ እንቅስቃሴ ውስጥ እንዲገቡ ማድረጉን ገልጸዋል። በተለይም በዲጂታሉ ዘርፍ በአቅም ግንባታ፣ በማማከርና ዲጂታል ሥርዓት በመገንባት በርካታ ሀገራት ድጋፍ ለማግኘት ፍላጎት አሳይተዋል ነው ያሉት። ፍላጎት ካሳዩ ሀገራት መካከል የተወሰኑት የመግባቢያ ስምምነቶችን ተፈራርመው ወደ የሙከራ ፕሮጀክት ትግበራ ለመሸጋገር የተዘጋጁ ሀገራት እንዳሉ ጠቁመዋል። በዚህም የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ቴክኖሎጂን በሙከራ ደረጃ በዛምቢያ፣ ሞዛምቢክ እና ቡሩንዲ ተግባራዊ ለማድረግ እንቅስቃሴ መጀመሩን ተናግረዋል። ይህ እንቅስቃሴ ተቋሙ አፍሪካውያን በራሳቸው አቅምና እርስ በርስ በመደጋገፍ የዲጂታል ሽግግርን ማሳካት እንደሚችሉ የሚያሳይና የደቡብ ለደቡብ ትብብርን ለማጠናከር ትልቅ ሚና የሚጫወት ነው ብለዋል። ኢትዮጵያም በአህጉራዊ ኢኒሼቲቮች ትግበራ አርዓያነት ያለው ሚናዋን እንድታጠናክር የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል።
ትናንትን በመማርና በማረም ዛሬን በላቀ ትጋት በመገንባት ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን የዕለት ተዕለት ባህላችን እየሆነ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 10, 2026 163
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ) ፦ ትናንትን በመማርና በማረም ዛሬን በላቀ ትጋት በመገንባት ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን የዕለት ተዕለት ባህላችን እየሆነ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጳጉሜን 5 የነገ ቀንን አስመልክቶ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው መልዕክት አስተላልፈዋል። በዚህ መልዕክታቸውም ከወረቀት ወደ ዲጂታል፤ ከተጠቃሚነት ወደ ፈጣሪነት ሲሉ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ትናንትን በመማርና በማረም ዛሬን በላቀ ትጋት በመገንባት ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን የዕለት ተዕለት ባህላችን እየሆነ ነው ብለዋል። ንግድና አገልግሎትን ያቀላጥፋል፣ መረጃዎችን ተደራሽ ያደርጋል፣ ዘርፎችንም ያዘምናል! ሲሉም ገልጸዋል። የ5 ሚሊዮን ኢትዮጵያ ኮደሮች ንቅናቄ ወጣቶችን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ፈጣሪ በማድረግ ወደ 7 ሚሊዮን ግባችን እያመራ ሲሆን የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነትና ጥራትን አረጋግጧል ብለዋል። በሀገር በቀል አቅም የበለጸገው የሳይበር ሉዓላዊነታችን ደግሞ የማንቆጣጠራቸው ቴክኖሎጂዎችን ጥገኝነት አላቆ በዲጂታል ኢኮኖሚ በራስ አቅሟ የምትቆም አዲሷ ኢትዮጵያ በታላቅ ምዕራፍ ላይ መሆኗን በኩራት ያበስራል ሲሉም ገልጸዋል።
የዲጂታል አብዮት ለነገዋ ኢትዮጵያ
Sep 9, 2026 409
በኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የታየው የቴክኖሎጂ ለውጥ የዛሬን ፈታኝ ሁኔታዎች ከመቅረፍ ባለፈ፣ ኢትዮጵያን ወደ ዘመናዊው የዲጂታል ምህዳር በፍጥነት እያሸጋገራት ይገኛል። የፖሊሲ ማሻሻያዎች፣ የዲጂታል መሰረተ ልማት ግንባታዎች እና የተቋማት ማጠናከሪያ ስራዎች ለዚሁ አገራዊ የነገ ትራንስፎርሜሽን በምሳሌነት የሚጠቀሱ ዋና ዋና እርምጃዎች ናቸው። መንግስት የዲጂታል ዘርፉን የሀገሪቱ የኢኮኖሚ እድገት ምሶሶ በማድረግ የነደፈውን "ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025" ስትራቴጂ በስኬት ማጠናቀቁ፣ 2030 ዲጂታል ስትራቴጂን መጀመሩ ሀገሪቱን በቴክኖሎጂው ዘርፍ ወደ አዲስ የወደፊት ምዕራፍ እንድትገባ ያስቻለ መሰረታዊ ለውጥ አምጥቷል። የቴሌኮም ዘርፉ ለውጭ ኢንቨስትመንት ክፍት መደረጉ፣ የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ መግባትና የኢትዮ ቴሌኮም መዘመን ለኢንተርኔት ተደራሽነት መስፋፋት ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል። በተለይም የ5G ቴክኖሎጂ አገልግሎት በስፋት መጀመሩ ሀገሪቱን በምስራቅ አፍሪካ በቴክኖሎጂ ተጠቃሚነትና በመሰረተ ልማት ዝግጁነት ቀዳሚ ያደረጋት ሲሆን፣ ይህም ለነገው ፈጣን የመረጃ ልውውጥ እና ለቀጣይ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎች ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል። የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማቱ መዘመን በፋይናንስ ዘርፉ ላይ አብዮታዊ ለውጥ በማምጣት የነገዋን ስማርት ኢኮኖሚ መደላደል ጥሏል። እንደ ቴሌብር ያሉ የዲጂታል ክፍያ አማራጮች በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች ያለ ባንክ ሂሳብ በስልካቸው ብቻ ግብይት እንዲፈጽሙ በማድረግ ለአካታች ዲጂታል ኢኮኖሚ ትልቅ አቅም ሆነዋል። ይህ የፋይናንስ ቴክኖሎጂ ምህዳር መስፋፋት ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች በቀላሉ የዲጂታል ክፍያዎችን እንዲቀበሉና የፋይናንስ ተደራሽነታቸው እንዲያድግ ያስቻለ ሲሆን፣ መደበኛ ያልሆነውን የግብይት ስርዓት ወደ ዘመናዊና ግልጽ የነገ ዲጂታል ስርዓት የመቀየር ሂደቱን አፋጥኖታል። በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) ረገድ የኢትዮጵያ ሰውሰራሽ አስተውሎት ኢንስቲትዩት መቋቋም የሀገሪቱን ታላቅ የነገ ራዕይ ለዓለም አሳይቷል። ኢንስቲትዩቱ በጤናው ዘርፍ የካንሰርና የሳምባ በሽታዎችን ቀድሞ የሚያውቁ የኤአይ ውጤቶችን በማበልጸግ ህይወትን የማዳን ስራ እያከናወነ ይገኛል። በተመሳሳይ በግብርናው ዘርፍ የአፈር ለምነትንና የሰብል በሽታን በቴክኖሎጂ የመለየት ስራዎች እየተከናወኑ ሲሆን፣ ይህም ለነገዋ ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትና ማረጋገጥና ለምርታማነት ማደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ሌላው ትልቅ የለውጡ ስኬት የሀገር በቀል ቋንቋዎችን በዲጂታል አለም ተወዳዳሪ ለማድረግ የተሰሩ የቋንቋ ፕሮሰሲንግ (NLP) ስራዎች ናቸው። ይህም የኢትዮጵያ ቋንቋዎች በዘመናዊ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎች ውስጥ እንዲካተቱ በማድረግ ለነገው ትውልድ የባህል እና የእውቀት መተላለፊያ ምቹ መንገድ ፈጥሯል። ከዚሁ ጎን ለጎን የ"ፋይዳ" (Fayda) ብሄራዊ ዲጂታል መታወቂያ ፕሮጀክት የዜጎችን መረጃ በማደራጀት ለነገው ዘመናዊ የአገልግሎት አሰጣጥ አስተማማኝ የመረጃ መሰረት ጥሏል። ይህም ለባንክ፣ ለጤናና ለሌሎች ማህበራዊ አገልግሎቶች ቀልጣፋ አሰራርን ፈጥሯል። በአሁኑ ወቅት ዜጎች እንደ ፓስፖርት ማደስ፣ የንግድ ፈቃድ ማውጣትና ግብር መክፈል ያሉ አገልግሎቶችን ከቤታቸው ሆነው በኢንተርኔት ማከናወን መቻላቸው የነገዋን አሰራር ዛሬ ማሳያ ሲሆን፣ የሳይንስ ሙዚየም ደግሞ የነገዎቹን ፈጣሪዎች አቅም የሚያበለጽግ ማዕከል ሆኗል። በተጨማሪም በዲጂታል ክህሎት ግንባታ ረገድ ለወጣቶችና ለባለሙያዎች የሚሰጡ የስልጠና ፕሮግራሞች በስፋት እየተካሄዱ ይገኛሉ። ይህም ኢትዮጵያ በነገው ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ መድረክ ብቁ እና ተወዳዳሪ የሆነ የሰው ኃይል እንድታፈራ ዘላቂ መሰረት እየጣለ ነው።
ነገን በብልሃት ማነጽ - የዲጂታል 2030 ስትራቴጂ
Sep 9, 2026 322
(በሙሴ መለሰ) ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የጀመረችውን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ አጠናክራ ለመቀጠል እና ከጊዜው ፈጣን የቴክኖሎጂ እድገት ጋር ለመራመድ “የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030” ስትራቴጂን በይፋ አድርጋለች። ታኅሣሥ 11 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ይፋ የተደረገው ይህ ታላቅ አገራዊ ዕቅድ፤ ሀገሪቱ በቴክኖሎጂው ዓለም ከተመልካችነት ይልቅ ተሳታፊና መሪ የምትሆንበትን አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው። ይህ አዲስ ስትራቴጂ ከቁጥሮች እና ከኢኮኖሚያዊ ስኬቶች ባሻገር፣ ዛሬን ከመቅረጽ ባለፈ ነገን ከመገንባት እና ለቀጣይ ትውልድ አሻራ ከማስቀመጥ አንጻር ሰፊና ጥልቅ ፋይዳ ያለው ሀገራዊ ትልም ነው። በዲጂታል ዘመን የመረጃ ሉዓላዊነት ከፍተኛ ትኩረት የሚሰጠው ጉዳይ ነው ። በዚህ ዘርፍ የሚያጋጥም ጥገኝነት የሃገር ደህንነት ላይም የራሱን አሉታዊ ተጽዕኖ ማሳረፉ አይቀርም። ‎ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በዚህ ዙሪያ መረጃ የዚህ ዘመን ስትራቴጂካዊ ሀብት እና ጠንካራ ሀገረ መንግሥት የሚገነባበት ቁልፍ የሉዓላዊነት ምሰሶ ነው ማለታቸው ይታወሳል። የተዋሰ አሊያም በውጭ አካላት ላይ ጥገኛ የሆነ መረጃ ሀገራዊ መሻታችንን ማሳካት ስለማያስችል፤ የፖሊሲ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የራስን መረጃ በራስ አቅም መሰብሰብ እና መተንተን ወሳኝ ግብዓት ነውም ብለዋል። የዲጂታል 2030 ስትራቴጂ ከወረቀት ባለፈ በህዝብና በሀገር ላይ የሚኖረው ተጨባጭ ማሳያ በአጭር ጊዜ ውስጥ መሬት የረገጠ እውነታ ነው። ለአብነት ያህል፣ በዓለም ሁለተኛውና ለአፍሪካ የመጀመሪያው የሆነው የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ ግንባታ መጀመሩ እና ከዩኤንዲፒ ጋር በመተባበር የተመረቀው 'AI UniPod' ማዕከል ለወጣቶች የተፈጠረ ትልቅ የቴክኖሎጂ መሠረት ነው። ተቋማቱ ከሀገር ውስጥ አልፎ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ተማሪዎች ነፃ የትምህርት ዕድል በማመቻቸት ላይ መሆናቸው፣ ኢትዮጵያ የአህጉሪቱ የፈጠራ ማዕከል ሆና እንድትቀጥል የሚያስችላት የትውልድ አሻራ ነው። የሞባይል ተጠቃሚዎችን ቁጥር 128 ሚሊዮን ለማድረስ እንዲሁም የ5G ኔትወርክ ተደራሽነትን ሙሉ በሙሉ እውን ለማድረግ የተነደፈው ዕቅድ፣ በከተማና በገጠር መካከል የነበረውን የዲጂታል ክፍተት በማጥበብ የመረጃ እኩልነትን የሚያረጋግጥ ትልቅ ምዕራፍ ነው። እንደ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ከመሳሰሉ መሠረተ ልማቶች ጋር ተቀናጅቶ የሚሰራው ይህ እቅድ፣ የዜጎችን ተደራሽነት በማስፋት እኩል እድል የሚፈጥር አሰራርን ይዘረጋል። ይህ የዲጂታል መረብ መስፋፋት የዜጎችን ኑሮ በጥራት ከማሻሻል ባለፈ አገልግሎቶች በፍጥነት እንዲቀላጠፉ ትልቅ አቅም ይፈጥራል። የመንግሥት አገልግሎቶችን ሙሉ በሙሉ ወረቀት አልባ ለማድረግ የሚከናወነው አሰራር ግልጽነትን በማስፈን በዜጎችና በተቋማት መካከል መተማመንን ያጎለብታል። ዲጂታል 2030 ስትራቴጂ የዛሬን ስኬት ብቻ ሳይሆን የወደፊቱን ትውልድ አዕምሮ በዕውቀትና በፈጠራ ብርሃን በመቅረጽ የሀገርን የሰው ሀብት በዘላቂነት የሚያለማ የዕድገት ምሰሶ ነው። ስትራቴጂው ካነጣጠረባቸው ቁልፍ ነጥቦች መካከል ተደራሽነትን ማስፋት፣ እኩል እድል መፍጠር እና በዜጎችና ተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት ይገኙበታል። ግልጽነት የሰፈነበት፣ ከወረቀትና ከቢሮክራሲ የጸዳ አሰራር መዘርጋቱ ዜጎች በሀገራቸው ተቋማት ላይ ያላቸውን እምነት ያጠናክራል። ይህ ደግሞ ማህበራዊ መተሳሰርን አጠናክሮ ለአንድነትና ለጋራ ብልጽግና መሰረት የሚጥል ትውልድ ተሻጋሪ ስራም ነው። በሚሊዮን የሚቆጠሩ የዲጂታል ሥራ ዕድሎችን ለወጣቶች ማመቻቸት የወጣቶችን ፈጠራ ወደ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም መቀየር ያስችላል። ወጣቱ በዲጂታል ንግድ፣ በሶፍትዌር ልማት እና በዲጂታል አገልግሎቶች ላይ ተሰማርቶ በራሱ ጥረት እያደገ ሲሄድ፣ የሀገሪቱ የኢኮኖሚ መሠረት የጸና ይሆናል። የዲጂታል ኢኮኖሚ እያደገ ሲሄድ የሳይበር ደህንነት እና የመረጃ ጥበቃ ወሳኝ ሚና ይጫወታሉ። የዲጂታል 2030 ስትራቴጂ የሳይበር ደህንነት መሠረተ ልማቶችን ማጠናከሩን እንደ ዋና ዕቅድ ይዞ መንቀሳቀሱ ዜጎችና ተቋማት በአስተማማኝ ዲጂታል ምህዳር ውስጥ እንዲኖሩ ያስችላል። ቴክኖሎጂ የሉዓላዊነት ሌላኛው መገለጫ በመሆኑ፣ የህዝብ ዲጂታል መሠረተ ልማትን ማስፋት ወሳኝ ነው። መረጃዎች በውጭ አካላት ቁጥጥር ስር ሲሆኑ የሀገር ደህንነት አደጋ ላይ ይወድቃል። የዲጂታል 2030 ስትራቴጂ የመረጃ ደህንነትን በአስተማማኝ ሁኔታ ለመጠበቅ የሚያስችል አቅም በመፍጠር ለነገው ትውልድ የባለቤትነት ስሜት ያጎናጸፋል። ወጣቶች በሮቦቲክስ፣ በዳታ ሳይንስ እና በሶፍትዌር ልማት ላይ ሲሰማሩ፣ ችግሮችን በፈጠራ ሃሳብ የሚፈቱ አዳዲስ ጅምሮች ይፈጠራሉ። ይህም የወጣቱን የእውቀት አቅምና ክህሎት ወደ ተጨባጭ ኢኮኖሚያዊ ውጤት በመቀየር ለቀጣዩ ትውልድ ራሱን የቻለ የኢኮኖሚ መሠረት ይጥላል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬት ከተቀናጀ የመደመር እሳቤ ጋር የሚተሳሰር ነው። ነገን የተረጋጋ ሰላምና ኢኮኖሚያዊ ብልጽግና የምናረጋግጥበት ሁነኛ መንገድም ጭምር ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም