ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎቱን ቀልጣፋና ተደራሽ ለማድረግ በዲጂታል ቴክኖሎጂ እያዘመነ ነው - ኢንጂነር አብዱልበር ሸምሱ
Sep 4, 2026 139
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎቱን ፈጣን፣ ቀልጣፋና ተደራሽ ለማድረግ በዲጂታል ቴክኖሎጂ እያዘመነ መሆኑን የድርጅቱ ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አብዱልበር ሸምሱ ገለጹ። የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ደንበኞች በዘመናዊ ዲጂታል አማራጭ የሚገለገሉበት የዲጂታል መተግበሪያ ዛሬ አስመረቋል። የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አብዱልበር ሸምሱ (ኢ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ዕድገት የሚያሳልጥ የባሕር ላይ የትራንስፖርት አገልግሎት እየተሰጠ ነው ብለዋል። በዚህም የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ለሀገሪቱ የሎጂስቲክስ ዘርፍ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት አሰራር እየተገበረ መሆኑን ተናግረዋል። ተቋሙ ለአፍሪካ ብቸኛ እና ታሪካዊ የባህር ትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪ ሆኖ መቆየቱን ገልጸው፤ በአሁኑ ወቅትም ዓለም አቀፍ ደረጃን የሚመጥን አዲስ አሰራር ስርዓት እየተገበረ ይገኛል ብለዋል። ዛሬ የተመረቀው ዲጂታል ቴክኖሎጂ ደንበኞች እንግልት በመቀነስ ረገድ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው እንዲሁም የኢኮኖሚ እንቅስቃሴውን የሚያፋጥን እንደሆነ አስታውቀዋል። በቀጣዮቹ ዓመታት ውስጥ ሙሉ ለሙሉ የሚጠናቀቁ ትላልቅ አዳዲስ ሲስተሞች እየተገነቡ መሆኑን ጨምረው አስታውቀዋል። በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተቋሙን ከዓለም አቀፍ አሰራሮች ጋር እኩል የሚያሰልፉ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ የቦርድ አባልና የኢትዮ-ጂቡቲ ባቡር ትራንስፖርት አክሲዮን ማህበር ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ታከለ ኡማ በበኩላቸው ፤ የሎጂስቲክስ ሥርዓቱን የሚያዘምን ሥራ እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህም መንግሥት የየብስ ትራንስፖርት፣ የባቡርና የደረቅ ወደብ መሠረተ ልማቶችን ከመገንባት ባለፈ፣ የመርከቦች ቁጥር እንዲበራከት እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የኢትዮጵያን የሎጂስቲክስ አቅም ለማጎልበት ከሚደረጉ ኢንቨስትመንቶች በተጨማሪም የባሕር በር ባለቤትነት ምላሽ ለማረጋገጥ በዋና አጀንዳነት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ የተመረቀው ዲጂታል ቴክኖሎጂም አገልግሎቱን ይበልጥ ለማሳለጥ ትልቅ ጥቅም እንደሚሰጥ አስታውቀዋል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ቅልጥፍናን ለማሳለጥ የቴክኖሎጂ አሠራር ወሳኝ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍራሆል ጣፋ ናቸው። የኢትዮጵያ ዲጂታል 2030 ስትራቴጂንና የሎጂስቲክስ ዘርፍ ስትራቴጂን መሠረት በማድረግ የሎጂስቲክስ ዘርፉን ለማዘመንና አሠራሩን ዲጂታላይዝ የሚያደርጉ በርካታ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። የዲጂታል መተግበሪያውም ግልጽ፣ ፈጣንና ዘመናዊ አሠራር ሥርዓትን ለመገንባት የሚያስችል ወሳኝ እርምጃ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢንስቲትዩቱ የሀገሪቱን የልማት ጉዞ የሚያፋጥን የሰው ሃይል የማፍራት ድርሻውን ያጠናክራል
Sep 4, 2026 124
ሃዋሳ ፤ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ) ፡-የፌደራል ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት ገበያ መር አዳዲስ ፕሮግራሞች በመክፈት የሀገሪቱን የልማት ጉዞ የሚያፋጥን የሰው ሃይል የማፍራት ድርሻውን እንደሚያጠናክር አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ በ2018 በጀት አመት አፈጻጸምና በቀጣይ እቅዶችና አቅጣጫዎች ላይ በሃዋሳ መክሯል።   የፌደራል ቴክኒክና ሙያ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት ኢንስቲትዩቱ ገበያ መር የሆኑ 11 አዳዲስ ፕሮግራሞችን በመክፈትና የተማሪዎች የቅበላ አቅሙን በማሳደግ የሀገሪቱን የልማት ጉዞ የሚያፋጥን የሰው ሃይል በማፍራት የበኩሉን እየተወጣ ነው ። ለዚህም አቅርቦት መር የነበረውን የስልጠና ሂደት ወደ ፍላጎት መር በመቀየር ዘመኑን የዋጁ የስልጠና ፕሮግራሞች ላይ እየተሰራ ነው ብለዋል። በሳይበር ሴኩሪቲ፣ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስና በባዮ ሜዲካል ቴክኖሎጂ ጥናትን መሰረት በማድረግ የስልጠና ዘርፎች መከፈታቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል። ኢንስቲትዩቱ የጥናትና ምርምር፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርና ኢንተርፕራይዝ ልማት ተግባራቱን ለማሳካት ከ17ዐ በላይ ኢንዱስትሪዎች ጋር ትስስር መፈጠሩንም አመልክተዋል። በበጀት አመቱም ከ40 በላይ የምርምር ስራዎችን በማድረግ ለፖሊሲ ግብአትና ለቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲያግዙ እንዲሁም ተኪ ምርቶችን ለማምረት አቅም የመፍጠር ስራ መሰራቱን ጠቁመዋል። በቀጣይም በኢንስቲትዩቱ የ10 አመት ስትራቴጂክ እቅድ ላይ መሰረት በማድረግ የቴክኒክና ሙያ ተቋማትን ችግር ፈቺ የፈጠራ ማእከላት የማድረጉ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል።   በምክትል ከንቲባ ማእረግ የሃዋሳ ከተማ አስተዳደር የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን መምሪያ ሃላፊ አቶ ቸርነት ፍላቴ በበኩላቸው በከተማው በተከናወኑ በርካታ የመሰረተ ልማት ስራዎች የቴክኒክና ሙያ ተቋማትና ባለሙያዎች በፈጠራ ስራ ጉልህ ድርሻ አበርክተዋል ብለዋል። የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ያወጧቸው የሰው ሀይልና የምርምር ስራዎች በከተማዋ እድገት የራሳቸውን ድርሻ ማበርከታቸውን ጠቁመዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል በኢንስቲትዩቱ የቴክስታይልና አፓሬል ፋሽን ቴክኖሎጂ ፋካሊቲ ዲን መረርቱ ዋቁማ (ዶ/ር) እንደገለፁት ኢንዱስትሪው የሚፈልገውን የሰው ሃይል ለማፍራት በመደበኛና በአጫጭር ስልጠናዎች በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። ፋሽን ቴክኖሎጂው የሚፈልገውንና ዘመኑን የዋጁ ፕሮግራሞችን በመክፈት የተጀመሩ ስራዎችን በማጠናከር ከዘርፉ የሚገኙ ጥቅሞችን የማሳደጉ ስራ እንደሚጠናከር አመላክተዋል ። በመድረኩ በቀረቡ የውይይት መነሻ ሰነዶችና የተቋሙ የ10 አመት ስትራቴጂክ እቅድ ላይ ውይይት ተደርጓል።          
ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ለአፍሪካ ሀገራት አቅም የሚሆን ውጤታማ ተግባራት እያከናወነች ነው
Sep 4, 2026 174
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ):- ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) ቴክኖሎጂ ለቀጣናው ብሎም ለአፍሪካ ሀገራት አቅም የሚሆን ውጤታማ ተግባራት እያከናወነች መሆኗን የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) ገለጹ። ዛሬ ነሐሴ 29 ቀን 2018 ዓ.ም ጨምሮ ለሁለት ቀናት የሚቆየው የኢጋድ አባል ሀገራት ተወካዮችና ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት፣ የቀጣናውን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ስትራቴጂ በጋራ ለመቅረጽ ያለመ አውደ ጥናት መካሄድ ጀምሯል።   የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ፈጣን ዕድገት የዓለም ኢኮኖሚን፣ መንግሥታትንና የሰውን አቅም እየቀረጸ ይገኛል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት እና የዲጂታል ዘርፍ የቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን በማፋጠን ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ወሳኝ ኃይል መሆኑንም ገልጸዋል። የምስራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) አባል ሀገራትም የሰው ሰራሽ አስተውሎት የቴክኖሎጂ አማራጭን በአግባቡ በመጠቀም የኢኮኖሚ ውህደትን ማፋጠን እንዳለባቸው ተናግረዋል። ለዚህም የሰው ሰራሽ አስተውሎት አጠቃቀም እና የመረጃ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ፣ ከአባል ሀገራት ብሔራዊ የሕግ ማዕቀፎች ጋር የተጣጣመ ቀጣናዊ የጋራ ቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋት እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል። አፍሪካ የሰው ሰራሽ አስተውሎትና የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ተጠቃሚነት ደረጃ ዝቅተኛ መሆኑን አንስተው፤ ዘርፉ በፍጥነት ለውጥ እያስመዘገበ ያለ መሆኑን ተናግረዋል። ስለሆነም ሀገራት ይህ ተግባር የህልውና ጉዳይ መሆኑን በመገንዘብ ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ በቀጣናው ብሎም በአፍሪካ ደረጃ በሰው ሰራሽ አስተውሎትና ቴክኖሎጂ የተሻለ እየሰራች መሆኑንም ጠቁመዋል። ኤ አይ ዩኒቨርሲቲን ጨምሮ ዘርፉን ለመምራት ኢንስቲትዩት በማቋቋም አበረታች ስራዎችን እያከናወነች መሆኑን ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲው ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለቀጣናው ብሎም ለአፍሪካ የሚጠቅም መሆኑንም አብራርተዋል። የኢጋድ አባል ሀገራቱ የተናበበ ፖሊሲ እንዲኖራቸውና የተሻሉ ተሞክሮዎችን ለማስፋት እየሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በቀጣይ ከቀጣናው የተውጣጡ ወጣቶችን የሚያሰለጥን የልህቀት ማዕከል ለማቋቋም እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል።   በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የኢጋድ ጉዳዮች ዳይሬክተር ከተማ ኃይሌ በበኩላቸው፤ ሰው ሰራሽ አስተውሎት የኢኮኖሚ እድገትን የሚያፋጥን ብዝኅ ምርታማነት አቅም መገንቢያ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል። በዚህም ሰው ሰራሽ አስተውሎትን ለቀጣናዊ ትብብር፣ ለጠንካራ የፖሊሲ ማዕቀፍ ዝግጅት፣ ለዲጂታል መሠረተ ልማት፣ እንዲሁም ለጥናትና ፈጠራ ኢንቨስትመንት መጠቀም እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ በሀገራዊ እና ቀጣናዊ ልማት ውስጥ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችና የሰው ሰራሽ አስተውሎትን ሚና በመገንዘብ ከኢጋድ አባል ሀገራት ጋር በትብብር ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ እየተገነባ ያለው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲም የኢጋድ አባል ሀገራትን እና አጠቃላይ አፍሪካን የሚጠቅም እንደሚሆን ገልጸዋል።  
የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ሥራን በእውቀትና በቴክኖሎጂ ታግዞ ለማከናወን አስችሎናል-ሰልጣኞች
Sep 4, 2026 131
ቦንጋ፣ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ሥራቸውን በእውቀት እና በቴክኖሎጂ ታግዘው ለማከናወን እንዳገዛቸው በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የመንግስት ሠራተኞች ገለፁ። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቪ የሆነው የ5 ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና ፕሮግራም የሀገሪቱን የዲጂታል ኢኮኖሚ ሽግግር በማፋጠን ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል። በፕሮግራሙም በዋናነት በሶፍትዌር ልማት፣ በዳታ ትንተና፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ክህሎት እና መሰል የቴክኖሎጂ ዘርፎች ላይ በማተኮር ለዜጎች ስልጠና እየተሰጠ ነው። ስልጠናውን በማስመልከት ኢዜአ ያነጋገራቸው በቦንጋ የትምህርት ኮሌጅ የፊዚክስ መምህር ሲሳይ አብደላ፣ መንግስት ባመቻቸው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በአራቱም ፕሮግራሞች ሰልጥናቸውን አጠናቀው የምስክር ወረቀት መውሰዳቸውን ተናግረዋል። ይህም ሥራቸውን በቴክኖሎጂ አስደግፈው ለማከናወን ከማገዝ ባለፈ በኦንላይን የራሳቸውን ሥራ ለመስራት ተነሳሽነት እንደፈጠረላቸው ጠቁመዋል።   ሌላው የስልጠና ዕድሉ ተጠቃሚ የመንግስት ሠራተኛ ወጣት ጌጥዬ አለሙ በበኩሉ በነጻ በተሰጠው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መሠረታዊ የዲጂታል እውቀቱን ማሳደጉ በስራው ተወዳዳሪ ለመሆን እንዳስቻለው ተናግሯል። በሶፍት ዌር ልማት፣ በዳታ ትንተና፣ በሞባይል አፕሊኬሽን ግንባታ እና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ሰልጥኖ ምስክር ወረቀት ማግኘቱ ሥራውን በተሻለ ጥራት ለማከናወን አስችሎታል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዜጎች በተለይ ወጣቶች ከቴክኖሎጂ ጋር እንዲተዋወቁና ክህሎታቸውን እንዲያዳብሩ ትልቅ እገዛ እያደረገ ነው ያሉት ደግሞ በቦንጋ ዩኒቨርሲቲ የሒሳብ መምህር ሙሉጌታ አንዷለም ናቸው።   በተለይ መምህራን ሥራቸውን ወቅቱ በደረሰበት የቴክኖሎጂ አውቀት ታግዘው እንዲያከናውኑ ያግዛቸዋል ብለዋል። በቀጣይ በዳታ ሳይንስ እና በአርቴፌሻል ኢንተለጀንስ ላይ ስፔሻላይዝ ለማድረግ ፍላጎት እንዳደረባቸውም ጠቁሟል ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ ምክትል ሀላፊና የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ዘርፍ ሀላፊ አቶ ምትኩ አሰፋው ኢንሼቲቩ ዲጅታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማፋጠን ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል።   እንደሀገር የተጀመረው የ5 ሚሊዮን ኮደርስ ኢንሼቲቪ በቴክኖሎጂ የበቃ ተወዳዳሪ ዜጋ መፍጠርን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ገልጸው፣ ስልጠናውን ለመውሰድ በክልሉ ከተመዘገቡት ውስጥ እስካሁን ድረስ ከ48 ሺህ በላይ የሚሆኑት ስልጠናውን አጠናቀው የምስክር ወረቀት ወስደዋል ብለዋል።          
የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ክህሎታችንን በማሳደግ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ አድርጎናል- ወጣቶች
Sep 4, 2026 82
ጎንደር፤ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ክህሎታችንን በማሳደግ ለስራ እድል ፈጠራ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለመሆን ከፍተኛ እገዛ እያደረገልን ነው ሲሉ ሰልጣኞች ገለጹ። በዚሁ ጉዳይ ላይ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የጎንደር ከተማ ወጣቶች እንዳሉት፣ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዘመኑ የሚጠይቀውን የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎታቸውን እና ተወዳዳሪነታቸውን አሳድጓል። አስተያየታቸውን ከሰጡ ወጣቶች መካከል በውሃ ምሕንድስና ሁለተኛ ዲግሪውን ያጠናቀቀው ዮሐንስ መልኬ ፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የመረጃ ትንተና እና የሰው ሰራሽ አስተውሎት ክህሎቴን ለማሳደግ አስችሎኛል ነው የሚለው። በትምህርት ወቅት የምርምር ስራ በሚያካሒድበት ወቅት መረጃዎችን በቀላሉ ለማደራጀት የተሻለ ክሕሎት እንዲኖረው በማድረጉ በአራት ነጥብ ውጤት ለመመረቅ እንደረዳውም ነው የተናገረው። በተሰማራበት የስራ መስክም ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ አሰራሮችን፣ የጤና አጠባበቅ እና የምግብ ስርዓትን በቀላሉ በመገንዘብ ምርታማነትን ለማሳደግ ስልጠናው የላቀ ሚና እንዳበረከተለት ነው ያረጋገጠው።   ወጣት ፍሬው ይግዛው በበኩሉ ከስልጠናው የሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI)፣ የፕሮግራሚንግ እና የመሰረታዊ ዳታ ሳይንስ እውቀትን በማግኘት በዲጂታል ቢዝነስ ዘርፍ ለመሰማራት እንደቻለ ነው የጠቀሰው። የኮደርስ ስልጠና በቴክኖሎጂው ዓለም አዳዲስ ግኝቶችን በቀላሉ ለመረዳት እና ከዓለም አቀፍ አሰራሮች ጋር አብሮ ለመራመድ የሚያስችሉ ዘመናዊ እሳቤዎችን ለመገንባት ትልቅ አቅም እንደፈጠረለትም ተናግሯል።   የጎንደር ከተማ አስተዳደር ስራ እና ክህሎት መምሪያ ተወካይ ኃላፊ አቶ አካሌ ፀጋይ እንደገለጹት፣ የኮደርስ ስልጠና በቴክኖሎጂ ዘርፍ እና በስራ እድል ፈጠራ የወጣቶችን ተጠቃሚነት እያሳደገ ይገኛል። የመንግስት ሰራተኞችን እና ወጣቶችን በስልጠናው በማሳተፍ የዲጂታል ክህሎታቸውን በማዳበር በሀገር ውስጥ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ በመሆን ተጨማሪ የስራ እድል እንዲያገኙ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም ስልጠናቸውን ላጠናቀቁ 44 ሺህ 962 ዜጎች የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ነው ያመለከቱት። በቀጣይም በከተማው የሚገኙ የመንግስት እና የግል ኮሌጆች የኮምፒውተር ክፍሎችን እና አሰልጣኝ መምህራንን በመጠቀም ስልጠናውን በስፋት ለማከናወን እንደሚሰራ አስረድተዋል።    
የሰው ሰራሽ አስተውሎት አጠቃቀምን ከአባል ሀገራት ብሔራዊ የሕግ ማዕቀፎች ጋር የተጣጣመ ቀጣናዊ የጋራ ቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋት ያስፈልጋል-ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር)
Sep 4, 2026 137
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ)፦ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አጠቃቀምንና የመረጃ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ከአባል ሀገራት ብሔራዊ የሕግ ማዕቀፎች ጋር የተጣጣመ ቀጣናዊ የጋራ ቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋት እንደሚያስፈልግ የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ገለጹ። ከዛሬ ነሐሴ 29 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ቀናት የሚቆየውና የኢጋድ አባል ሀገራት ተወካዮችና ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት፣ የቀጣናውን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ስትራቴጂ በጋራ ለመቅረጽ ያለመ አውደ ጥናት መካሄድ ጀምሯል።   የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ፈጣን ዕድገት የዓለም ኢኮኖሚን፣ መንግሥታትንና የሰውን አቅም እየቀረጸ ይገኛል። ሰው ሰራሽ አስተውሎት እና የዲጂታል ዘርፍ የቀጣናዊ ኢኮኖሚ ውህደትን በማፋጠን ለማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ወሳኝ ኃይል መሆኑንም ገልጸዋል። የምሥራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) አባል ሀገራትም የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ አማራጭን በአግባቡ በመጠቀም የኢኮኖሚ ውህደትን ማፋጠን እንዳለባቸው ተናግረዋል። ለዚህም የሰው ሰራሽ አስተውሎት አጠቃቀም እና የመረጃ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ፣ ከአባል ሀገራት ብሔራዊ የሕግ ማዕቀፎች ጋር የተጣጣመ ቀጣናዊ የጋራ ቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋት እንደሚገባ አሳስበዋል። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የኢጋድ ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ከተማ ኃይሌ በበኩላቸው፤ ሰው ሰራሽ አስተውሎት የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥንና ብዝኅ ምርታማነት አቅም መገንቢያ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል። በዚህም ሰው ሰራሽ አስተውሎትን ለቀጣናዊ ትብብር፣ ለጠንካራ የፖሊሲ ማዕቀፍ ዝግጅት፣ ለዲጂታል መሠረተ ልማት፣ እንዲሁም ለጥናትና ፈጠራ ኢንቨስትመንት መጠቀም እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ በሀገራዊ እና ቀጠናዊ ልማት ውስጥ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችንና የሰው ሰራሽ አስተውሎትን ሚና በመገንዘብ ከኢጋድ አባል ሀገራት ጋር በትብብር ለመሥራት ቁርጠኛ መሆኗንም ተናግረዋል። በኢትዮጵያ እየተገነባ ያለው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲም የኢጋድ አባል ሀገራትን እና አጠቃላይ አፍሪካን የሚጠቅም እንደሚሆን ገልጸዋል።
መተግበሪያው የኢትዮጵያ 2030 የዲጂታል ጉዞ ግቦች ዕውን እንዲሆኑ የራሱን አስተዋጽኦ ያበረክታል- ኢንጂነር ታከለ ኡማ
Sep 4, 2026 267
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ)፡-የዲጂታል መተግበሪያው መጀመር የኢትዮጵያ 2030 የዲጂታል ጉዞ ግቦች ዕውን እንዲሆኑ የራሱን አስተዋጽኦ የሚያበረክትበት ምዕራፍ መሆኑን የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ቦርድ አባል እና የኢትዮ-ጂቡቲ ባቡር ትራንስፖርት አክሲዮን ማህበር ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ታከለ ኡማ ገለጹ። የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ደንበኞች በዘመናዊ ዲጂታል አማራጭ የሚገለገሉበት የዲጂታል መተግበሪያ ዛሬ አስመረቋል።   የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ የቦርድ አባልና የኢትዮ-ጂቡቲ ባቡር ትራንስፖርት አክሲዮን ማህበር ዋና ስራ አስፈጻሚ ታከለ ኡማ (ኢ/ር) ፤ ዛሬ የሚጀምረው ቴክኖሎጂ ትልቅ ትርጉም ያለውና ደንበኞች የተሻለ እንዲሁም ውጤታማ አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል። መንግስት የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ የምስራቅ አፍሪካ ትልቅ ተቋም እንዲሆን እንደሚፈልግ አንስተዋል። ይህንንም ለማስቻል በርካታ ውጤታማ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። ይፋ የተደረገው የዲጂታል አገልግሎት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ጉዞን ለማሳካት የተያዙ ግቦች ዕውን እንዲሆኑ የራሱን ሚና የሚወጣበት ምዕራፍ መሆኑን ገልጸዋል።   የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዋና ስራ አስፈጻሚ አብዱልበር ሸምሱ (ኢ/ር) በበኩላቸው፤ ድርጅቱ እያደገ ያለውን ኢኮኖሚ የሚመጥን አገልግሎት ለመስጠት አሰራሩን እያዘመነ ይገኛል። አገልግሎት አሰጣጡን ፈጣን፣ ቀልጣፋና ተደራሽነት ለማረጋገጥ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ ትኩረት ማድረጉን አስታውቀዋል። ዛሬ የተመረቀው የዲጂታል መተግበሪያ የአገልግሎት አሰጣጡን የበለጠ በማዘመን ለደንበኞች ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል ገልጸዋል። ደንበኞች በመተግበሪያው አማካኝነት በሞባይል ስልካቸው እንዲመዘገቡ፣ የሂደት ክትትል እንዲያደርጉ እና ተያያዥ አገልግሎቶችን በፍጥነትና በምቾት እንዲያገኙ ያስችላል ብለዋል። በቀጣይም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለማድረግና ውጤታማ አገልግሎት ለመስጠት የዲጂታል ቴክኖሎጂ የማጠናከር ተግባር እንደሚቀጥል ገልጸዋል።  
የአዳማ ከተማ የኢንቨስትመንት ፍሰትን ለማሳደግ የአገልግሎት አሰጣጡን ዲጂታላይዝ አድርጓል
Sep 3, 2026 140
አዳማ ፤ነሐሴ 28/2018(ኢዜአ )፡-የአዳማ ከተማ አስተዳደር የኢንቨስትመንት ፍሰትን ለማሳደግ የመሰረተ ልማትና የአገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታላይዝ ማድረጉን የአስተዳደሩ ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ ገለፁ። በከተማዋ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች የተሰማሩ ባለሃብቶች የተሳተፉበት ፎረም ተካሄዷል ።   የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ እንደገለፁት፣ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን በስፋት ለማሳደግ ከተማ አስተዳደሩ በዋናነት ትኩረት አድርጎ እየሰራ ይገኛል። የሕዝብ ወይም የተቋማት አገልግሎት አሰጣጥን ይበልጥ ዘመናዊ፣ ፈጣን እና ቀልጣፋ ለማድረግ ዋናው ትኩረት የተደረገው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ላይ ነው ብለዋል። በዚህም በከተማዋ ኢንቨስትመንትን በማስፋፋት ለወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር፣ እንዲሁም ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማትን ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።   የአዳማ ከተማ ኢንቨስትመንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ሐሲያ ኢሳ በበኩላቸው፤ በከተማዋ ኢንቨስትመንትን በማበረታታት ምርቶችን ለውጭ ገበያ ለማቅረብና የተኪ ምርቶችን ለማሳደግ በተደረገው እንቅስቃሴ አበረታች ውጤት መገኘቱን ገልጸዋል። በዚህም ዘርፉ የግንባታና የፍጆታ ምርቶችን በማምረት ገበያውን ለማረጋጋት በሚደረገው ጥረት ውስጥ የጎላ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የአዳማ ከተማ የኢንቨስተሮች ፎረም አስተባባሪ አቶ ፈይሳ አራርሳ በበኩላቸው፤ ፎረሙ በባለሀብቶችና በአስተዳሩ መካከል ያለውን ትስስር በማጠናከር የመሠረተ ልማትና የመሬት አቅርቦት ጥያቄዎችን በትብብር ለመፍታት እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የከተማዋን የኢንቨስትመንት ፍሰት ለማሳለጥና የባለሀብቶችን ተሳትፎ ለማጠናከር ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን አስረድተዋል። ከፎረሙ ተሳታፊዎች መካከል የኩሩፍቱ የወረቀት ፋብሪካ ተወካይ አቶ ሲሳይ ጌታቸው፤ መንግሥት ባለሀብቶች በፍጥነት ወደ ሥራ እንዲገቡ ለማስቻል የኢንቨስትመንት መሬትና የመሠረተ ልማት ጥያቄዎችን በወቅቱ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል።    
በአማራ ክልል የቴክኖሎጂውን ዘርፍ ቁልፍ የእድገት መሳሪያ ለማድረግ እየተሰራ ነው - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Sep 3, 2026 336
ባህርዳር ፤ ነሃሴ 28/2018 (ኢዜአ) ፦ በአማራ ክልል የቴክኖሎጂውን ዘርፍ ቁልፍ የእድገትና የመወዳደሪያ መሳሪያ አድርጎ ለመጠቀም በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለጹ። በክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ "የኤሌክትሮኒክስ መንግስት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 መሰረት ነው" በሚል መሪ ቃል የፓናል የውይይት በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። ርዕሰ መስተዳደሩ በውይይቱ ላይ እንደገለጹት፣ በክልሉ ፈጠራና ቴክኖሎጂን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አቅም ማሳለጫ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። በአማራ ክልል "ዲጂታል አማራ" በሚል በ25 ዓመቱ የዕድገት እና ትራንስፎርሜሽን ፍኖተ ካርታ ላይ ቴክኖሎጂ እንደ ልማት መዳረሻ መፍጠሪያ ተደርጎ ተይዟል ብለዋል። በ25 ዓመቱ ስትራቴጂክ ግብ ላይ በ2042 የአማራ ክልል ዋነኛ ሀብት፤ የአገልግሎት መስጫ እና የኢኮኖሚ የዕድገት ምንጭ ቴክኖሎጂ እንዲሆን ይሠራል ነው ያሉት። በዚህም ዘርፉን የሚመራውን ተቋም በአዲስ በማደራጀት፣ አሰራሮችን በመዘርጋትና አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱን አስረድተዋል። በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ላይ በቴክኖሎጂና ዲጂታላይዜሽን የታገዘ ፈጣን፣ ቀልጣፋና ከብልሹ አሰራር የጸዳ አገልግሎት ለመስጠት ያስቻለ ውጤት መመዝገቡን አስረድተዋል። በቀጣይም ተቋማት ቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ የማምረትና አገልግሎት የመስጠት ተግባር ላይ አተኩረው እንዲሰሩ አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግም አስገንዝበዋል። የኢፌዴሪ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶር) በበኩላቸው፣ በቴክኖሎጂና ፈጠራ ላይ በትኩረት በመስራት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025ን ማሳካት ተችሏል ብለዋል። ባለፈው አፈጻጻም የተገኘውን ተሞክሮ በመቀመርም አሁን ላይ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙ አስረድተዋል። የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማትን በማሟላት የዲጂታል ግብይት፣ ከወረቀት ንክኪ ነጻ የሆነ የመንግስት አገልግሎትና ጉልበት የቀነሰ አመራረት እውን በማድረግ ለውጥ መመዝገቡንም አስረድተዋል። ይህም የሰው ኃይሉን በኢትዮ ኮደርስ በማሰልጠን ጭምር በተሰማራበት የስራ ዘርፍ ሁሉ ውጤታማና በዓለም አቀፍ ጭምር ተወዳዳሪ እንዲሆን በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በአገራችን የሚገኘው ወጣት ኃይል ራሱን በቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት በማነጽ እየመጣ ያለውን ዓለም አቀፍ ውድድር ለማሸነፍ መዘጋጀት እንዳለበት አሳስበዋል። በፓናል ውይይቱ ላይ የፌዴራልና የክልል የዘርፉ አመራሮችና ባለሙያዎች የተሳተፉ ሲሆን በእለቱም የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ያዘጋጀው የቴክኖሎጂ ውጤቶች አውደ ርዕይ ለእይታ ክፍት ተደርጓል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የደንበኞችን ቁጥር በማሳደግና የዲጂታል አገልግሎቶችን በማስፋፋት ተጨባጭ ውጤቶች ተገኝተዋል
Sep 3, 2026 368
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የደንበኞችን ቁጥር በማሳደግና የዲጂታል አገልግሎቶችን በማስፋፋት ተጨባጭ ውጤቶች መገኘታቸውን የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ። ኢትዮ ቴሌኮም የ2019 በጀት ዓመት ዕቅዱን አስመልክቶ ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል።   ኩባንያው ባለፈው የ2018 በጀት ዓመት ያስመዘገበውን ስኬት መነሻ በማድረግ፣ በ2019 ዓ.ም የደንበኞቹን ቁጥር ለማሳደግ፣ ገቢውን ለማሳደግ እና የዲጂታል አገልግሎቶችን ለማስፋፋት በርካታ ግቦችን ማቀዱን አስታውቋል። የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ በመግለጫው እንደተናገሩት በ2019 በጀት ዓመት የቴሌኮም መሰረተ ልማትን ይበልጥ ለማዘመን የ5G እና 4G የኔትወርክ ተደራሽነትን ለማሳደግ ታቅዷል። ተቋሙ ባለፈው አንድ ዓመት የደንበኞችን ቁጥር በማሳደግና የዲጂታል አገልግሎቶችን በማስፋፋት አበረታች ውጤቶች ማስመዝገቡን ገልጸዋል። በ2019 በጀት ዓመት የሀገሪቱን የዲጂታል ኢኮኖሚ ይበልጥ የሚያንቀሳቅሱ አዳዲስ አሰራሮችና አገልግሎቶች እንደሚተገበሩ ተናግረው፤ 295 ቢሊዮን ብር ገቢ ለማግኘት መታቀዱን ገልጸዋል። በ2019 ዕቅድ የትምህርት፣ የጤናና ሌሎች ማህበራዊ አገልግሎቶችን በዲጂታል መንገድ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች በቀላሉ ተደራሽ ለማድረግ እንደሚሰራ አስታውቀዋል። በበጀት ዓመቱ 1ሺህ 628 ተጨማሪ አዳዲስ የሞባይል ጣቢያዎች የሚገነቡ ሲሆን፣ ከእነዚህም ውስጥ 605 ያህሉ በሀገሪቱ ገጠራማ አካባቢዎችና የቴሌኮም አገልግሎት ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች መሆኑን አብራርተዋል። የ4G አገልግሎት ለተጨማሪ 300 ከተሞች ተደራሽ የሚደረግ ሲሆን፣ ይህም የአገልግሎቱን ተደራሽነት 95 በመቶ ያደርሰዋል ብለዋል። የ5G አገልግሎት ለተጨማሪ 40 ከተሞች እንደሚዳረስና በአጠቃላይ የ5G ተጠቃሚ ከተሞች ቁጥር ወደ 83 ከፍ ይላል ብለዋል። ተቋሙ ባደረገው ከፍተኛ ኢንቨስትመንት ተጨማሪ 20 ሚሊዮን ደንበኞችን ማስተናገድ የሚያስችል የገመድ አልባ ሞባይል ኔትወርክ አቅም በመፍጠር፣ አጠቃላይ የማስተናገድ አቅሙን ወደ 135 ነጥብ 7 ሚሊዮን ያሳድጋል ብለዋል። በፊክስድ ብሮድባንድ አገልግሎት ላይ የሚታዩ የአገልግሎት መቋረጦችን ለማስወገድና የአገልግሎት ጥራትን ከፍ ለማድረግ ተጨማሪ 150 ሺህ ደንበኞችን የተሻለ የፋይበር ቴክኖሎጂ የማዛወር ስራ እንደሚከናወን አብራርተዋል። በከተሞች የሚገኘውን የፋይበር መስመር በመጨመር 300 ኪሎ ሜትር በማስፋፋት አጠቃላይ አቅሙን ከ15 ሺህ ኪሎሜትር በላይ ከፍ ለማድረግ ማቀዱን አስታውቀዋል። ኢትዮ ቴሌኮም ያስቀመጣቸውን እነዚህን ግቦች ለማሳካት የቴክኖሎጂ አጋርነቱን እንደሚያጠናክር እና በሰው ሃይል ልማት ላይ ትኩረት አድርጎ እንደሚሰራ አስገንዝበዋል።
በአማራ ክልል ዲጂታል 2030ን በተሳካ መልኩ እውን ለማድረግ እየተሰራ ነው
Sep 3, 2026 134
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ዲጂታል 2030ን በተሳካ መልኩ እውን ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ገለፀ። በባሕር ዳር ከተማ የቴክኖሎጂ የፈጠራ ሥራዎችን የሚያሳይ አውደ ርዕይ ተከፍቷል።   በአውደ ርዕዩ የመክፈቻ ላይ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ አረጋ ከበደ፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) እና ሌሎች የፌደራልና የክልል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የአማራ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ የቻለ ይግዛው እንደገለጹት፤ የኤግዚቢሽኑ ዋና ዓላማ በክልሉ ዲጂታል 2030 ን እውን ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን ማሳየትና ማስተዋወቅ ነው። አውደ ርዕዩ በዘርፉ የተሰማሩ አካላት የፈጠራ ሥራዎቻቸውንና የቴክኖሎጂ ውጤቶቻቸውን ለሕዝብና ለተጠቃሚዎች የሚያቀርቡበት ዕድል እንደሚፈጥርላቸው አብራርተዋል። ይህም የቴክኖሎጂ ፈጠራን በማስፋፋት የተያዘውን ሀገራዊና ክልላዊ የዲጂታላይዜሽን ግብ ለማሳካት እየተሠራ መሆኑን የሚያመላክት ነው ብለዋል። በተጨማሪም በኤግዚቢሽኑ በተለያዩ ተቋማት የለሙ 35 የተለያዩ ዲጂታል ሥርዓቶች (Digital Systems) በይፋ ተመርቀው ወደ ሥራ እንደሚገቡ አስታውቀዋል።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት ምዕራብ፣ ሰሜን ምዕራብ፣ደቡብ ምዕራብና መካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ይኖራቸዋል
Sep 2, 2026 684
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ) ፦ በሚቀጥሉት አስር ቀናት ምዕራብ፣ሰሜን ምዕራብ፣ደቡብ ምዕራብ እና መካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖራቸው የኢትዮጵያ የሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ከነሃሴ 26 ቀን ጀምሮ እስከ ጳጉሜን አምስት ቀን 2018ዓ.ም ድረስ በኢትዮጵያ የሚኖረውን የአየር ፀባይ ሁኔታ በተመለከተ ለኢዜአ መግለጫ ልኳል። በመግለጫውም ነሀሴ ወር የክረምት የመጨረሻ ወቅት በመሆኑ በሰሜን ምሥራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች የዝናብ መጠን እንደሚቀንስ በማመላከት ለረጅም ጊዜ ደረቅ ሆነው የሰነበቱት ደቡብና ደቡብ ምሥራቅ አካባቢዎች ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸውን እንደሚያስተናግዱ ጠቁሟል። በምሥራቅ፣ በሰሜን ምሥራቅና በመካከለኛው ኢትዮጵያ አካባቢዎች የዝናብ መጠንና ስርጭት እንደሚቀነስ ነገር ግን በደቡብና ደቡብ ምሥራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች በስርጭትም በመጠንም የተሻለ ዝናብ እንደሚያገኙ በመግለጫው ተመላክቷል። በሚቀጥሉት አስር ቀናትም ምዕራብ፣ሰሜን ምዕራብ፣ደቡብ ምዕራብ እና መካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖራቸው ይጠበቃል። ማኅበረሰቡም ከላይ በተጠቀሱት ቦታዎች ላይ የሚኖረውን የእርጥበት ሁኔታ ታሳቢ ባደረገ መልኩ የግብርና ስራቹን እንዲያከናውን ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል። ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው እርጥበት ከሚያስተናግዱ ቦታዎች መካከል ቄለም ወለጋ፣ ኢሉባቦር የምዕራብ ፣መካከለኛ ፣ደቡብ እና ሰሜን ጎንደር፣ የሰሜን፣ የምዕራብ እና ምሥራቅ ጎጃም ዞኖች፣ ካማሺ፣ መተከል፣ አሶሳ ዞኖች እንደሚገኙበት ከመግለጫው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል። ሁሉም ሸዋ ዞኖች፣ አኝዋክ፣ ከፋ፣ ምዕራብ ኦሞ፣ ጉራጌ ፣አዲስ አበባ ፣ድሬዳዋ፣ የምዕራብ ፣የሰሜን ምዕራብ ፣መካከለኛው፣ ምሥራቅ እና ደቡብ ትግራይ ዞኖች ፣የሲዳማ አብዛኛው የክልሉ ዞኖች ደግሞ ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ከሚያስተናግዱ አካባቢዎች መካከል መሆናቸው ተጠቁሟል። ኢንስቲትዩቱ ቀላል፣መካከለኛ እና ከባድ እርጥበትን የሚያስተናግዱ የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ፣ የመኸር ሰብል አብቃይ ፣ አርብቶ አድርና ከፊል አርብቶ አደር አካባቢዎች የሚገኙ የማኅበረሰብ ክፍሎች ይህን የአየር ሁኔታ ለግብርና ስራዎቻቸው እንዲያውሉ አስገንዝቧል። ይህ በእንዲህ እንዳለ መካከለኛ እና ከባድ የዝናብ መጠን የሚያስተናግዱ አካባቢዎች ተደፋታማ ማሳዎች ላይ የተዘጉ የማፋሰሻና የማንጣፈፊያ ቦዮች ክፍት እንዲሆኑ ማድረግ፣ የሰብል በሽታን አረምን አስቀድሞ መከላከል ፣የአፈር መሸርሸር ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራት ማከናወን፣ እና አርሶ አደሮችም የማሳ ጉብኝት በየጊዜው በማድረግ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባም አሳስቧል። ከቀላል እስከ መካከለኛ እርጥበት የሚያገኙ ቦታዎች ደግሞ የሚገኘውን እርጥበት በአግባቡ ጥቅም ላይ ማዋል፣ የዝናብ ውሀን በማሰባሰብ በደረቅ ወቅቶች መጠቀም ፣የአፈር ውስጥ ትነትን መጠንን ለመቀነስ የሚያስችሉ ተግባራትን ማከናወን ፣የእንስሳት ግጦሽ ሳርን በአግባቡ መያዝ ተገቢ ነውም ተብሏል። ለተከታታይ አስር ቀናት የሚቆየው አየር ፀባይ ሁኔታም የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የሀገሪቱ ተፋሰሶች ላይ ከዝቅተኛ እስከ ከፍተኛ መጠን ያለው የገፀ ምድር የውሃ ፍሰት እንደሚኖራቸው ኢንስቲትዩቱ ገልጿል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን በሰብል ዝርያዎች ምርምርና በመነሻ ዘር ብዜት በትኩረት እየተሰራ ነው
Sep 2, 2026 163
መተማ፣ ነሐሴ27/2018 (ኢዜአ):- በምዕራብ ጎንደር ዞን የግብርና ምርትና ምርታማነትን በዘላቂነት ለማሳደግ በሰብል ዝርያዎች ምርምርና በመነሻ ዘር ብዜት ተግባራት ላይ በማተኮር እየተሰራ እንደሚገኝ የጎንደር ግብርና ምርምር ማዕከል አስታወቀ። ማዕከሉ እያካሔደ ባለው የዘር ብዜትና ማላመድ ስራ ላይ ያተኮረ የጉብኝት መርሃ ግብር ዛሬ ተካሂዷል። በማዕከሉ የቅባትና ጭረት ሰብሎች ምርምር ባለሙያ አቶ እንዳልካቸው አክሊሉ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ማዕከሉ የደጋ፣ ወይና ደጋና ቆላማ አካባቢዎች የሰብል ምርታማነት ለማሳደግ እየሰራ ይገኛል። የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎችን ለማውጣት፣ ለማላመድ ፣ ለሰብል አያያዝና ጥበቃ ላይ ያተኮሩ የምርምር ስራዎችን በማከናወን ምርታማነትን በማሳደግ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዚህም በያዝነው ክረምት በምዕራብ ጎንደር ቆላማ አካባቢዎች በ100 ሄክታር መሬት ላይ 17 የሰብል አይነቶች የዘር ብዜት እያከናወነ እንደሚገኝ አስረድተዋል።   ከሁለት ሺህ ኩንታል በላይ ዘር ለዘር አባዥ አርሶ አደሮችና ተቋማት በመስጠት የዘር ብዜትና የማላመድ ተግባሩን በስፋት እያከናወነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በዚህም በቅርቡ ምርታማነታቸው ተረጋግጦ ይፋ የተደረጉትን "መልካም" የማሽላ፣ "ጠረፍ ወርቅ" የአኩሪ አተር፣ "ማርዘነብ" የሰሊጥና "ጃንተከል" የጥጥ ዝርያን ወደ አርሶ አደሩ ለማድረስ እየተሰራ ነው ብለዋል። በተጨማሪም በማዕከሉ የማሽላ፣ ሰሊጥ ፣ አኩሪ አተር፣ የፈረንጅ ሱፍ ፣ ለውዝ ፣ ጤፍና በቆሎ የመነሻ ዘር ብዜት ስራዎች እያካሄደ መሆኑን ጠቁመው፤ ጉብኝቱም የጀመረውን ተግባር ለማስፋት የሚያስችል ነው። በማዕከሉ የሩዝ ሰብል ምርምር ባለሙያ አቶ አሳየ ብርሃኑ እንዳሉት፤ የሩዝ ሰብልን ከፎገራና አካባቢው ባሻገር በምዕራብ ጎንደር ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ስጦታ በመጠቀም ለማስፋት እየተሰራ ነው ብለዋል። ባለፉት ዓመታት ምርታማነታቸው የተሻሻሉ "ሚሪካ4" እና "አዝመራ" የተሰኙ የሰሊጥ ዝርያዎችን ማቅረባቸውን ጠቁመው፤ አሁን በሄክታር እስከ 60 ኩንታል የሚሰጥ "ፎገራ1" የተሰኘ ዘር እያባዙ መሆኑን ተናግረዋል። የዛሬው ጉብኝትም በዞኑ በሰፋፊ እርሻ ቦታዎች ሩዝን ለማልማት የሚያስችል እየተደረገ ያለውን ጥረት አመራሩና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገንዝበው እንዲደግፉ ለማድረግ ያለመ ነው ብለዋል። የመተማ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ምህረት ፈቃዱ በበኩላቸው፤ ማዕከሉ ባለፉት ሰባት ዓመታት በምርጥ ዘር ብዜትና አዳዲስ ዝርያዎችን በማስተዋወቅ ምርታማነት ለማሳደግ ጥረት አድርጓል ነው ያሉት። በተለይም በምርምር የተገኘውን "መልካም" የተሰኘ የማሽላ ምርጥ ዘር በማቅረብ ቀደም ሲል በሄክታር ከ16 ኩንታል የነበረውን ምርታማነት ወደ 40 ኩንታል እንዲያድግ ማስቻሉን አውስተዋል። ወረዳውም ማዕከሉ የምርምር ስራውን ለማስፋፋት እያደረገ ያለውን ጥረት በመደገፍ ለወጭ ንግድና ለኢንዱስትሪ ግብአት የሚሆን ምርት ለማምረት የተያዘውን ግብ ለማሳካት እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በመስክ ጉብኝቱ የተሳተፉት አቶ መስፍን አበራ በበኩላቸው፤ የምርምር ማዕከሉ እያደረገ ያለው የዘር ብዜትና የማላመድ ተግባር በዘርፉ የተሰማሩ አርሶ አደሮችና ባለሃብቶችን ተጠቃሚ ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። "በማዕከሉ ድጋፍ እየተባዛ ያለው ሰብል ቁመና እጅግ አስደሳች ነው" ያሉት አቶ መስፍን፤ ይህም የምርምር ስራው ውጤታማነትን ያረጋገጠ መሆኑን መመልከታቸውን አስረድተዋል።  
ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን እያሳደገ የሚገኘው ኮደርስ
Sep 2, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የኮደርስ ስልጠና ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር ለመራመድና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገላቸው መሆኑን ስልጠናውን ያጠናቀቁ ተማሪዎች ገለፁ። የ''አምስት ሚሊየን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ’’ ስልጠና ሐምሌ 2016 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ይፋ መደረጉ ይታወሳል። መርሃ ግብሩ በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት 5 ሚሊየን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት እንዲጨብጡ ለማስቻል ያለመ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተያዘው ክረምት ወቅት የ5 ሚሊየን የኮደርስ መርሐ ግብር ወደ 7 ሚሊየን ከፍ ለማድረግ ጥሪ ማቅረባቸውም ይታወሳል። የኮደርስ ስልጠናን የተከታተሉ ሰልጣኞች ለኢዜአ እንዳሉት ስልጠናው ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል። በኮተቤ ሳይንስ ሼርድ ካምፓስ የ11ኛ ክፍል ተማሪ የሆነችው ዕፁብ የወንድወሰን ስልጠናን በተመቸ ጊዜ መውሰድ የሚቻልና ከክፍያ ነፃ የሆነ ዕድል መሆኑን ተናግራለች። ስልጠናው ከዘመኑ ጋር ለመራመድ የሚያስችል ራስን ማብቂያ መንገድ ነውም ብላለች። በሳውዝ ዌስት አካዳሚ የ11ኛ ክፍል ተማሪ የሆነው ነቢዩ ዳዊት፣ ከትምህርት ሰዓቱ ጋር በማጣጣም በቀን ለ30 ደቂቃ ያህል ስልጠናውን በመከታተል ማጠናቀቁን ገልጿል።   ሌሎችም ወጣቶች የኮደርስን ስልጠናን በመውሰድ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነታቸውን ማሳደግ እንዳለባቸው ጠቁሟል። የአዲስ አበባ ከተማ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ቱሉ ጥላሁን (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት እንደ ሀገር የኮደሮችን ቁጥር ወደ 7 ሚሊየን ለማድረስ የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት እየተሰራ ነው። ቀደም ሲል በአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያን ኮደርስ እቅድ ለአዲስ አበባ የተመደበው 809 ሺህ ለማሰልጠን እንደነበርና ሀገራዊ እድቀዱ ወደ ሰባት ሚሊዮን ማደጉን ተከትሎ ወደ 1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ከፍ ማለቱን አንስተዋል።   እስካሁን ባለው ለመመዝገብ ከታቀደው ውስጥ ወደ 985 ሺህ ዜጎች መመዝገባቸውንና ከእነዚህ ውስጥም 871 ሺህ ስልጠናቸውን አጠናቅቀው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ቢሮው የተለያዩ መድረኮችን በመጠቀም የግንዛቤ ስራዎችን በማከናወንና ከተቋማት ጋር በመቀናጀት ዕቅዱን ለማሳካት እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። በቀሪ ጊዜያትም የተማሪዎች ላብራቶሪዎችን፣ የወጣቶች ማዕከላትን፣ ቤተ መጻሕፍትን እና የተለያዩ የማህበረሰብ መድረኮችን በመጠቀም ዕቅዱን ለማሳካት ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂክ ትግበራ በብዙ ዘርፎች ለመጣው እድገት የላቀ አስተዋጽኦ አበርክቷል- ምሁራን
Sep 1, 2026 332
ዲላ ፤ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፡- የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂክ ትግበራ በብዙ ዘርፎች ለመጣው እድገትና ለተመዘገበው ስኬት የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የዘርፉ ምሁራን ገለጹ። ኢትዮጵያ የዲጅታል 2025 ስትራቴጂክ ትግበራ በስኬት በማጠናቀቅ ወደ ሌላ ምእራፍ በመሸጋገር የዲጅታል 2030 ትግበራ በማከናወን ላይ ትገኛለች። የስትራቴጂክ ትግበራው በዘርፉ በብዙ መልኩ የሚገለፅ እመርታ የተመዘገበ ሲሆን ለተለያዩ ሴክተሮችም የዲጅታል ትግበራና ማንሰራራት ወሳኝ ምእራፍ የከፈተ ሆኗል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የዘርፉ ምሁራን የዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂክ ትግበራ በብዙ ዘርፎች ለመጣው እድገትና ለተመዘገበው ስኬት የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። የዘርፉ ልማት ከተለያዩ ሴክተሮች ተግባራዊ እንቅስቃሴ ጋር በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የሚገናኝ መሆኑን ያነሱት ምሁራኑ በተለይም ትምህርት እና ጤናን ጨምሮ የተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች የሚጨበጥ ውጤት ማምጣት አስችሏል ብለዋል።   በዲላ ዩኒቨርሲቲ የኢንዱስትሪ ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክተር አዲሱ ፍርንጆ (ዶ/ር)፤ የዲጂታል መሰረተ ልማት ከግንባታ ጀምሮ እሰከ ትግበራ ድረስ በጥቂት አመታት በመንግስት የተከናወነው ስራ እና የመጣው ውጤት አስደናቂ መሆኑን አንስተዋል። የፋይዳ መታወቂያ፣ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎትና ሌሎችም ተያያዥ ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች ለዜጎች ፈጣን አገልግሎትና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል ማሳቻሉን አንስተዋል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናም በተለይም ወጣቶች በዘርፉ የካበተ እውቀት እንዲኖራቸውና ብቁ ተወዳዳሪ ሆነው የስራ እድል እንዲፈጠርላቸው ያደረገ መሆኑን አንስተዋል። የዘርፉ ልማት ለብዙ ሴክተሮች እድገትና ማንሰራራት መሰረት መሆኑን አንስተው በዲጅታል ዘርፍ በጥቂት አመታት የታየው ስኬት የኢትዮጵያን መፃኢ እድል በግልጽ የሚያመላክት መሆኑን አስረድተዋል። የዩኒቨርሲቲው በርካታ አገልግሎቶች በዲጂታል እየተከናወኑ መሆኑን አንስተው በዘርፉ የወጣቶችን የፈጠራ አቅም ለማሳደግ በሰው ስራሽ አስተውሎትና በሮቦትክስ ዘርፍ ስልጠና እየተሰጠ ስለመሆኑም ተናግረዋል። በዩኒቨርሲቲው የኮምፒዮተር ሳይንስ መምህርና ተመራማሪ እንዲሁም የማህበረሰብ አገልግሎት ዲጂታላይዜሽንና የውጭ ፕሮጀክት ዘርፍ ሃላፊ ሰናይት ሞቲ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራ በፋይናንስ ስርዓት፣ በአገልግሎትና ሌሎችም ዘርፎች የፈጠረው አቅም ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል።   የዲጂታል ሥርዓት የአገልግሎት አሰጣጥና የአኗኗር ዘይቤ እየሆነ መምጣቱን አንስተው መልዕክት ከመለዋወጥ ጀምሮ የትኛውንም አገልግሎት ለመስጠትና ለማግኘት ከወረቀት ንክኪ ነጻ የማድረግ ስራ እየተስፋፋ ይገኛል ብለዋል። የከፍተኛ የትምህርት ተቋማትም የዲጅታል ትግበራ ማዕከል በመሆን በዘርፉ የማህበረሰቡን ግንዛቤ በማሳደግ የዲጂታል 2030 እውን ለማድረግ እየሰሩ መሆኑን አንስተዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ትግበራ በአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና አስተዳደራዊ ዘርፎች ላይ መሰረታዊ እመርታዊ ለውጥ ማምጣቱ ይታወቃል።
የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሚጠይቀውን የዲጂታል ክህሎት የታጠቀ ትውልድ ማፍራት እያስቻለ ነው - አቶ ሚሊዮን ማቲዎስ
Aug 30, 2026 408
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት በኢትዮ-ኮደርስ የአምስት ሚሊየን ስልጠና መርሃ ግብር በዲጂታል ዕውቀትና ክህሎት የበለፀገ የሰው ሃይል ለማፍራት በትኩረት እንደሚሰራ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ሚሊዮን ማቲዎስ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቀጣይ አምስት ዓመትና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ በየደረጃው ባሉ የከተማ አስተዳደሩ የሥራ ኃላፊዎች ውይይት እየተደረገበት ነው።   የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የከተማ አስተዳደሩ ተቋማት ባለፉት አምስት ዓመት በስትራቴጂክ ዕቅድ የመፈጸም ቁርጠኝነታቸውን በቀጣዮቹ ዓመታትም አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ አሳስበዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሚሊዮን ማቲዎስ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የወጣቶችን ተሳትፎና ፈጠራ ማበረታታት ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው። ባለፉት አምስት ዓመታትም ከ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ የመዲናዋ ዜጎችን የሥራ ዕድል በመፍጠር የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ እንደተቻለ ገልጸዋል። በዚህም የአዲስ አበባ ወጣቶች በግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ኮንስትራክሽን፣ አገልግሎትናበሌሎች ዘርፎች ተጠቃሚ የሚሆኑበት ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል። በቀጣይም የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አጫጭርና መካከለኛ ሥልጠና በመስጠት ለኢንተርፕራይዞች በቂ የገንዘብ ብድር አቅርቦት እንደሚመቻች አስረድተዋል። የአዲስ አበባን የዓለም የዲፕሎማሲ ከተማነት የሚመጥንና ዘመኑ የደረሰበትን የቴክኖሎጂ ልህቀት የታጠቀ ወጣት የሰው ሃይል ለማፍራት እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል። የኢትዮ-ኮደርስ የአምስት ሚሊዮን ስልጠና መርሃ ግብር ይፋ በተደረገ ማግስት ከአንድ ሚሊዮን የሚበልጡ ወጣቶች የሥልጠናው ተካፋይ መሆናቸውን አስታውቀዋል። በሚቀጥሉት አምስት ዓመታትም ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ የመዲናዋ ዜጎች ስልጠና በመስጠት በየትኛውም የዓለም ጫፍ የበይነ መረብ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚሰራ አስታውቀዋል። በዚህም የ21ኛው ክፍለ ዘመን የቴክኖሎጂና ዲጂታል ሥምሪት የሚጠይቀውን ዕውቀትና ክህሎት የተላበሰ ወጣት ለማፍራት የኮደርስ ሥልጠና ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።   የአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ደሳለኝ ተረፈ በበኩላቸው፤ የአዲስ መሶብ አንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት በተቋቋመ ማግስት የተገልጋዮችን እርካታ ከ99 በመቶ በላይ ማድረስ አስችሏል ብለዋል። በመዲናዋ በ11 ማዕከላት 25 የአዲስ አበባና የፌዴራል ተቋማት 150 አገልግሎቶችን እየሰጡ መሆኑን ገልጸው፤ እስከ መስከረም ወር ተጨማሪ ማዕከላት ይገነባሉ ብለዋል። በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የአገልግሎት አሰጣጡን ከእርካታ ወደ አመኔታ የማሸጋገር ዕቅድ መያዙን በማንሳት፤ የመንግሥት አገልግሎቶችን በተለያዩ አማራጮች እንደሚሰጥ ገልጸዋል።  
የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ማደግና ዲጂታላይዜሽን የዜጎችን የአኗኗር ዘይቤ እያሻሻለ ነው
Aug 29, 2026 224
ቦንጋ ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ማደግና ዲጂታላይዜሽን የዜጎችን የአኗኗር ዘይቤ እያሻሻለ ነው ሲሉ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የቦንጋ ከተማ ነዋሪ ምሁራን ገለጹ። የመደመር መንግሥት ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሀገሪቱን የኢኮኖሚ እድገት ለማፋጠንና አገልግሎቶችን ለማዘመን የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን በተግባር ማየታቸውንም ምሁራኑ ተናግረዋል። የኮሌጁ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መምህር ምስጋናው ታደሰ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ የዲጂታላይዜሽን ትግበራ የሀገር ልማትን ፣ የኢኮኖሚ ዕድገትን፣ የመንግሥት አሠራር ብቃትን ማሳደጊያ እና የዜጎችን ኑሮ ማሻሻያ መሣሪያ ነው። የመደመር መንግሥት ለዲጂታላይዜሽን በሰጠው ልዩ ትኩረት ውስጥ ተግባራዊ የተደረገው የዲጂታል 2025 እስትራቴጂ የዜጎችን የአኗኗር ሁኔታ በተጨባጭ ማሻሻሉንም ነው ምሁሩ የተናገሩት። በዚህ እስትራቴጂ በሞባይል ባንኪንግ፣ በቴሌኮሙኒኬሽን፣ በኦንላይን አገልግሎቶችና በዲጂታል መታወቂያ ዘርፎች የተመዘገቡ ለውጦች ዜጎች የተለያዩ አገልግሎቶችን በቀላሉና በተፋጠነ መንገድ እንዲያገኙ ያደረጉ መሆኑን አንስተዋል። በኢኮኖሚው ዘርፍም አዳዲስ የንግድ ዕድሎችን የፈጠረ ሲሆን የዚሁ አካል የሆነው የ‘ኢትዮ-ኮደርስ’ ፕሮግራም ወጣቶችን የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ብቻ ከመሆን ባለፈ የቴክኖሎጂ ፈጣሪ እንዲሆኑ ትልቅ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። በመሆኑም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 የተገኙ አበረታች ውጤቶች ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ጠንካራ መሠረት የጣሉ መሆናቸውን አስረድተዋል። ባለፉት ዓመታት በዘርፉ የተከናወኑት ተግባራት ዲጂታል ኢኮኖሚውን በማስፋፋት የዜጎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሻሻላቸውን የገለጹት ደግሞ የኮሌጁ የመረጃ ቴክኖሎጂ መምህር ታደሰ ዘውዴ ናቸው። ከዚህ ውስጥም የ‘መሶብ’ የአንድ ማዕከል አሠራር የመንግሥት አገልግሎቶችን ተደራሽነት በማሻሻል ዜጎች ጊዜና ወጪያቸውን በቆጠበ መልኩ የተለያዩ አገልግሎቶችን እንዲያገኙ ያደረገ መሆኑንም ለአብነት አንስተዋል። የዲጂታል 2025 መጠናቀቅን ተከትሎ የተተገበረው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በኢኮኖሚው ዘርፍና በማኅበረሰቡ ውስጥ ሰፊ ለውጥ የሚያመጣ መሆኑንም ነው የገለጹት።
በአማራ ክልል የመሶብ አንድ ማዕከልን ጨምሮ ከ35 በላይ የዲጂታል አሰራሮችን ለመዘርጋት ተችሏል- ቢሮው
Aug 28, 2026 197
ባህር ዳር፡ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የመሶብ አንድ ማዕከልን ጨምሮ ከ35 በላይ የዲጂታል አሰራሮችን በመዘርጋት ቀልጣፋና ከብልሹ አሰራር የጸዳ አገልግሎት መስጠት መቻሉን የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ የቻለ ይግዛው ባለፉት ሦስት ዓመታት በዲጂታላይዜሽን ትግበራ በተመዘገቡ ውጤቶችና በቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ዛሬመግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም የመሶብ አንድ ማዕከላትን ጨምሮ የተለያዩ ዘመናዊ መተግበሪያዎችን በማልማት ለህብረተሰቡ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት ተችሏል። የክልሉ መንግሥት በ25 ዓመት የስትራቴጂክና አሻጋሪ ዕቅዱ ለቴክኖሎጂው ዘርፍ በሰጠው ትኩረት መሠረት፣ አገልግሎት በሚበዛባቸው ተቋማት ላይ በማተኮር ከ35 በላይ የዲጂታል አሰራሮች መዘርጋቱን ነው የገለጹት። ቴክኖሎጂዎቹ በፍትሕ ሥርዓት፣ በፕሮጀክቶች አፈጻጸም፣ ኢንቨስትመንት በመሳብና በግብርናው ዘርፍ ላይ አዎንታዊ ለውጥ እንዲመጣ ማስቻላቸውንም አብራርተዋል። በተጨማሪም ቴክኖሎጂዎቹ የመንግሥት አካላት በተጨባጭ መረጃ ላይ የተመሠረተ ውሳኔ እንዲሰጡ ከማድረጋቸው ባሻገር፣ ይስተዋሉ የነበሩ ብልሹ አሰራሮችን ለማስወገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን አስረድተዋል። በተለይም "መሶብ" የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በክልል ደረጃ በባህር ዳር፣ ደሴና ወልዲያ ከተሞች ተግባራዊ በማድረግ የህዝቡን እርካታ ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል። በተካሄደው የዳሰሳ ጥናትም እስካሁን ከ103 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች በመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት በኩል ፈጣን ፣ ፍትሐዊና ከብልሹ አሰራር የጸዳ አገልግሎት ማግኘታቸው መረጋገጡን አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅትም የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎትን ወደ ሌሎች ከተሞች ለማስፋት የግንባታና የቴክኖሎጂ ዝርጋታ ሥራው እየተፋጠነ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። በቀጣይ ዓመትም የዲጂታል 2030ን ግብ ለማሳካት ተጨማሪ ከ13 በላይ አዳዲስ መተግበሪያዎችን የማልማት ስራ እንደሚከናወን አብራርተዋል። በክልሉ በዲጂታል ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራትን ለህዝብ ለማስተዋወቅ ያለመ የፓናል ውይይትና የኤግዚቢሽን መርሃ-ግብር ከነሐሴ 28 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም በባህር ዳር ከተማ እንደሚካሄድ ተመላክቷል።  
የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ጉባዔ ኢትዮጵያ በክትባትና በጤና ምርምር ዘርፍ ያስመዘገበቻቸውን ውጤቶች ለማስተዋወቅ ምቹ አጋጣሚ ፈጥሯል
Aug 28, 2026 270
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ጉባዔ ኢትዮጵያ በክትባትና በጤና ምርምር ዘርፍ ያስመዘገበቻቸውን ውጤታማ ተግባራት ለማስተዋወቅ ምቹ አጋጣሚ መፍጠሩን የአርማወር ሀንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ ገለጹ። በአዲስ አበባ ለሶስት ቀናት ሲካሄድ የቆየው 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባዔ በትናንትናው ዕለት በስኬት መጠናቀቁ ይታወቃል፡፡ የጉባዔው ተሳታፊዎች በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ የሚገኘውን የአርማወር ሀንሰን የምርምር ኢንስቲትዩትን በመጎብኘት በሥራ ላይ ያሉ አቅሞችንና የምርምር ሥራዎችን ተመልክተዋል፡፡   የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በጉባዔው በጤና ምርምር ዘርፎች ያስመዘገበቻቸውን ውጤታማ ተግባራት ለአህጉሩ ተወካዮች ማጋራት ችላለች፡፡ በመድረኩ በጤና መረጃ ሥርዓት ትንተና፣ በአቅም ግንባታ እና በክትባት ዙሪያ ያስመዘገበቻቸውን ስኬቶች አጋርታለች ብለዋል፡፡ ተጨባጭ ስኬቶቿን እንድታሳይ ከማስቻሉም በላይ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጋር የጠበቀ የላቦራቶሪና የምርምር ትስስር እንድትፈጥር ማስቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ የጋራ ልምድ ለመለዋወጥ ትልቅ ዕድል መፍጠሩንም እንዲሁ፡፡ በጉባዔው ወቅት የቀረቡት የምርምርና የአቅም ግንባታ ሥርዓቶች በቀጣይ ለሚከናወኑ ሀገራዊና አህጉራዊ የጤና ሥራዎች በበጎ መነሻነት የሚያገለግሉ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ ጉባዔው ለኢትዮጵያም ሆነ ለተሳታፊ ሀገራት የጋራ ተጠቃሚነትን ያረጋገጠ መልካም አጋጣሚ እንደነበር አብራርተዋል፡፡   በጋምቢያ የጤና ሚኒስቴር የጤና አገልግሎት ዳይሬክተር (ዶ/ር) ሞሞዶ ንያሲ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ የጤና ሥርዓት ሂደቱ እጅግ ፈጣንና በትክክለኛው አቅጣጫ ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡ በተለይ የአርማወር ሀንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት ለአጠቃላይ የአፍሪካ አህጉር የሚመጥን ትልቅ የልህቀት ማዕከል መሆኑን አብራርተዋል፡፡ ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት የህክምና ባለሙያዎቻቸውንና ተመራማሪዎቻቸውን ለልምድ ልውውጥ፣ ለምርምር፣ ለፈጠራ ሥራዎችና ለትምህርት ሊልኩበት የሚችሉበት ተስፋ ሰጪ ኢንስቲትዩት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የአፍሪካን የጤና አጀንዳ በተሻለ ደረጃ ለማሳካትና አህጉራዊ ችግሮችን በጋራ ለመፍታት ከኢንስቲትዩቱ ጋር የጠበቀና የተቀናጀ የትብብር ግንኙነት ለመሥራት በጉጉት እንደሚጠብቁም ተናግረዋል፡፡
የስፔሻላይዝድ የውሃ ላቦራቶሪው የውሃ ጥራትን በማስጠበቅ የምርመራና ምርምር አቅም ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ ይኖረዋል
Aug 27, 2026 664
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የስፔሻላይዝድ የውሃ ላቦራቶሪው የውሃ ጥራትን በማስጠበቅ የምርመራና ምርምር አቅም ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው የኢትዮጵያ ውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ የውኃ ጥራት ምርመራንና ምርምርን ለማጠናከር የተገነባውን ስፔሻላይዝድ የውኃ ምርመራ ላቦራቶሪ ዛሬ አስመርቋል።   የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ታመና ኃይሉ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የውኃ ጥራትን በተሟላ መልኩ መመርመር የሕዝብ ጤናን ከመጠበቅ ባሻገር የውኃ ሀብትን በዘላቂነት ለመጠቀም የላቀ ሚና አለው። ላቦራቶሪው የሕክምናና የውኃ ማጣሪያ ሂደቶችን በተገቢው ለመምራትና የሀገሪቱን የምርመራ አቅም ለማሳደግ ወሳኝ መሆኑንም ገልጸዋል። በተለይም ለመጠጥ፣ ለመስኖና ለኢንዱስትሪ የሚውል ውኃ ተገቢውን የጥራት ደረጃ እንደሚያሟላ ለመለየት ምርመራ የሚያካሂድ ሲሆን፣ የውኃ ምርመራ ውጤቶችን በአንድ ቦታ በማሰባሰብ ለምርምርና ለዕውቀት ማከማቻ ለማዋል ያስችላል ብለዋል። አንድ የውኃ ምንጭ በአንድ ወቅት ንጹሕ መሆኑ በሌላ ወቅትም ተመሳሳይ ጥራት እንዳለው አያረጋግጥም። በመሆኑም የውኃ ጥራት በየጊዜው በመመርመር ውጤቶቹ በዳታ መልክ መመዝገብና ለተለያዩ የልማትና የምርምር ሥራዎች መዋል እንዳለበት ጠቁመዋል። በላቦራቶሪው በኩል በሀገሪቱ በተበታተነ መልኩ የሚገኙ የላቦራቶሪ አቅሞችን በማስተሳሰር፣ ባለሙያዎችን በማሰልጠንና በአይኤስኦ ደረጃዎች የተመሠረተ የምርመራ ሥርዓት በመዘርጋት የሀገሪቱን የላቦራቶሪ አቅም ለማጠናከር እንደሚሠራም ተገልጿል።   በኢንስቲትዩት የሥራ አመራር ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጀምበርነሽ ክንፈ በበኩላቸው፣ የውኃ ናሙና እና ምርመራ የሚወጣውን የውጭ ምንዛሬ ለማስቀረት ላቦራቶሪው ወሳኝ ሚና እንዳለው ተናግረዋል። ላቦራቶሪው ከውኃ ጥራት ምርመራ በተጨማሪ የውኃ ጥራት ምርምርና ሥልጠና እንዲሁም ከአቅም በላይ የሆኑ ምርመራዎችን በማከናወን እንደ ሪፈራል ላቦራቶሪ ሊያገለግል እንደሚችልም አስረድተዋል። በተጨማሪም የተፋሰስና የምሥራቅ አፍሪካ ሀገራት የውኃ ናሙናዎችን ወደ ኢትዮጵያ በማምጣት እንዲያስመረምሩና ከውኃ ጋር ተያያዥ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ ዕድል እንደሚፈጥርም ጠቁመዋል። ላቦራቶሪው በሙሉ አቅሙ ሥራ ሲጀምር የውኃ ጥራትን ከማረጋገጥ ባለፈ የምርምር፣ የሥልጠና፣ የገቢ ማመንጫና የውኃ ዲፕሎማሲ ማዕከል ሆኖ ያገለግላል ሲሉም ተናግረዋል።   ላቦራቶሪው በውኃ ውስጥ የሚገኙ ኬሚካላዊ፣ አካላዊና ማይክሮባዮሎጂያዊ ይዘቶችን በመመርመር የውኃ ጥራትን ለማረጋገጥ ያግዛል ያሉት ደግሞ የውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የስፔሻላይዝድ ላቦራቶሪ መሪ ሥራ አስፈጻሚ አብዱረህማን ሰይድ ናቸው። ቀደም ሲል በሀገር ውስጥ ባሉ ላቦራቶሪዎች ሊከናወኑ ያልቻሉ አንዳንድ ምርመራዎች ወደ ውጭ በመላክ ይከናወኑ እንደነበር ጠቁመው፣ የምርመራ ውጤት ለማግኘት የሚወስደውን ጊዜም ያሳጥራል ብለዋል። በውኃ ውስጥ የሚገኙ ኬሚካሎች ወይም ጎጂ ማይክሮኦርጋኒዝሞች ከተፈቀደው መጠን በላይ መኖራቸው በሰው ጤና ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ሊያሳድር ስለሚችል፣ የውኃ ጥራትን በላቦራቶሪ መፈተሽ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸዋል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም