ሳይንስና ቴክኖሎጂ
መገናኛ ብዙሃን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በመታገዝ ብሔራዊ ጥቅምን ለማስከበር መስራት ይገባቸዋል
Jun 14, 2025 98
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ መገናኛ ብዙሃን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በመታገዝ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር መስራት እንዳለባቸው የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ገለጹ። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት እና እሁድ ኤ.አይ ስቱዲዮ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ አሰራር ጥበብ ያሰለጠኗቸውን 25 የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች አስመርቀዋል።   ሰልጣኞቹ ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት፣ ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን፣ ከኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እና ከፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን የተውጣጡ ናቸው። የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎቹ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ በመታገዝ በይዘት ስራዎች ላይ እሴት መጨመር የሚያስችል የጽንሰ ሃሳብና የተግባር ተኮር ስልጠና የወሰዱ ናቸው። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በምርቃት መርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ ስልጠናው በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ ኢትዮጵያን ወደ ፊት የሚወስድ ነው። በመሆኑም ሰልጣኞች የተማሩትን ወደ ተግባር በመለወጥ ሀገርን ለመቀየር የመስራት ሃላፊነት እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል። ህብረ ብሔራዊ አንድነትን ለማጠናከር፣ ብሔራዊ ጥቅምን ለማስከበር፣ የወል ትርክትን ለመፍጠርና ሀገርን ለማበልጸግ የተያዙ ዋና ዋና እቅዶችን ለማሳካት ቴክኖሊጂውን ጥቅም ላይ በመዋል መስራት ይገባል ብለዋል። በተመሳሳይ በተማሩበት ሙያ ብሔራዊ ጥቅምን የሚያስጠብቁ ፊልሞችን በማምረት፣ ሌሎች ሙያተኞችን በማሰልጠን፣ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ ጽንሰ ሃሳብን ግንዛቤ በመፍጠር መስራት እንደሚገባቸውም አስገንዝበዋል። የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ የደረሰበትን ደረጃ በመረዳትና በመገናኛ ብዙሃን የይዘት ስራዎች ውስጥ በመጠቀም ለህብረ ብሔራዊ አንድነት ማጠናከርና ብሔራዊ ጥቅምን ለማስከበር ማዋል እንደሚገባ በአጽኖኦት አንስተዋል። የመገናኛ ብዙሃን ኃላፊዎችም ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ እውቀት እንዲስፋፋ መስራት እንዳለባቸው በማስገንዘብ ተቋማትን በአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች የማዘመን ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት።   የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነብዩ ባዬ በበኩላቸው የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በአግባቡ መጠቀም በድህረ እውነት በሀገር ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ለመከላከል ይረዳል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት እየተሰራ ለሚገኘው የአሰባሳቢ ትርክት ግንባታም አጋዥ መሆኑን ጠቅሰው፤ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የፈጠራ ስራዎችን ለመደገፍ እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።   የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና(ኢ/ር ዶ/ር) በበኩላቸው የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂን በመጠቀም እንደ ሀገር ትልቅ ለውጥ ማምጣት ይቻላል ብለዋል። ኢትዮጵያ ዓለም ከደረሰበት የቴክኖሎጂ ደረጃ ጋር ለመሄድ በርካታ ተግባራትን እያከናወነች መሆኑን ጠቁመው፤ መገናኛ ብዙሃንም ለዘርፉ ትኩረት በመስጠት መስራት እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል።   በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች የወሰዱት ስልጠና ለይዘትና ሌሎች ስራዎች ትልቅ አቅም በመፍጠር የሀገርን ጥቅም ለማስጠበቅ ፋይዳው ትልቅ መሆኑንም የመገናኛ ብዙሃን ኃላፊዎች ተናግረዋል።   በመሆኑም በተቋሞቻቸው በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ የታገዙ ስራዎችን ለመስራት ምቹ ሁኔታዎችን እንደሚፈጥሩ አረጋግጠዋል። ሰልጣኞቹ በበኩላቸው በስልጠናው ያገኙትን እውቀት የሀገራቸውን ጥቅም ለማስጠበቅ እንደሚያውሉ ገልጸዋል።
ቋሚ ኤግዚቢሽኑ ከዓለም ፈጣን የቴክኖሎጂ ዕድገት ጋር የሚያወዳድር ነው
Jun 14, 2025 54
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ በሳይንስ ሙዚየም የተከፈተው ቋሚ ኤግዚቢሽን ኢትዮጵያን ከዓለም ፈጣን የቴክኖሎጂ ዕድገት ጋር የሚያወዳድርና የትውልዱን መጻዒ ዕድል በፈጠራና ምርምር የሚያግዝ መሆኑን የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽንን በይፋ ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ነገን መስራት፣ ማየት እና መለማመድ የሚፈልጉ ሰዎች በሙሉ የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽንን እየመጡ መመልከት አለባቸው ብለዋል። ኢትዮጵያውያን ነገን መስራት ነገን መለወጥ ከፈለጉ ልጆቻቸውን ወደ ኤግዚቢሽኑ ሊያመጧቸው እንደሚገባም አመልክተዋል። ልጆቻችንም ይህ ትልቅ ዕድል እንደሆነ ተገንዝበው ክረምቱን ይህንን ቋሚ ኤግዚቢሽን በማየት ብዙ ትምህርት መቅሰም አለባቸው ሲሉም ገልጸዋል። ኤግዚቢሽኑ በውስጡ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የአካባቢ፣ የግብርና፣ የውሃና ኢነርጂ፣ የስፔስና አቪየሽን ማሳያ ክፍሎችን አካቷል። በዕለቱ ቋሚ ኤግዚቢሽኑን የቱሪዝም፣ የኪነ ጥበብ፣ የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎችና ታዋቂ ግለሰቦች ጎብኝተውታል። አስተያየታቸውን የሰጡ ጎብኚዎችም ኢትዮጵያ በሳይንስና ቴክኖሎጂ እንዲሁም በሰው ሰራሽ አስተውሎት ባከናወነቻቸው ሥራዎች መደመማቸውን ነው ያነሱት። የኦሮሚያ ቱሪዝም ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ነጋ ወዳጆ ቴክኖሎጂን በአግባቡ መጠቀም ከተቻለ ምን ያህል ውጤታማ ሊያደርግ እንደሚችል ያየንበት ነው ብለዋል። ሰው ሰራሽ አስተውሎት በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርትና በሌሎች ዘርፎች አጋዥ በመሆኑ ትውልዱ ሳይንስን በአግባቡ በመረዳት ለአዳዲስ ፈጠራዎች እንዲተጋ የሚያግዝ መሆኑንም አመልክተዋል።   የፍሎውረስ ኢቨንትስ ስራ አስኪያጅ ዮአዳን ጥላሁን በበኩላቸው እንደገለጹት፤ የቋሚ ኤግዚቢሽኑ መከፈት ተማሪዎች ሳይንስ ላይ የተመሰረተ ተጨባጭ ፊልምና ትርኢት የማየት ዕድል እንዲያገኙና ከቴክኖሎጂ ጋር በደንብ እንዲተዋወቁ ያስችላል። በቋሚ ኤግዚቢሽኑ ኢትዮጵያን በዓለም ተወዳዳሪ የሚያደርጉ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን አይቻለሁ የሚሉት ደግሞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ረዳት መምህር ማስተር ምህረት ከድር ናቸው።   ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬ በበኩሏ፤ በሳይንስ ሙዚየም በቴክኖሎጂ የታገዘ የፈጠራ ትርኢትና ፊልም በአድናቆት መመልከቷን ገልጻለች። ቋሚ ኤግዚቢሽኑ ትልቋ ኢትዮጵያን ከማሳየት ባለፈ የተፈጥሮ ጸጋ፣ የእድገትና የቴክኖሎጂ ልህቀት መሻቷን የሚያሳይ እንዲሁም ለተማሪዎች የነገ ተስፋ ለተመራማሪዎች ደግሞ ምቹና ሁሉን ያቀፈ ማዕከል መሆኑን ነው ያብራራችው።   ጋዜጠኛ ዮናስ ከበደ በሙዚየሙ የትናንት፣ የዛሬና የነገ ማንነታችንን ያየንበት ነው ብሏል። ኢትዮጵያ አሁን ላይ የደረሰችበት ከፍታ ትናንትን ያልረሳና ትውልድን ያስተሳሰረ መሆኑ ሁሉንም የሚያኮራ መሆኑን በማንሳት።   ጋዜጠኛ ዳዊት አበበም የሰው ሰራሽ አስተውሎት የሰው ልጆችን ህይወት በማቅለል በኩል የደረሰበትን ደረጃ በቀላሉ ማየትና በዚያ መጠቀም የሚያስችሉ ዕድሎች መፈጠራቸውን አድንቋል።   የሳይንስ ሙዚየምን በሰለጠኑ ሀገራት የመመልከት ዕድል እንደነበረውና በአጭር ጊዜ በኢትዮጵያ እውን ሆኖ ማየቱ አግራሞት እንደፈጠረበት የገለጸው ደግሞ አርቲስት ዳንኤል ተገኝ ነው። በሙዚየሙ ያገኘውን ዕድል ተጠቅሞ ለሀገርና ህዝብ ጠቃሚ የሆነ ፊልም ለመስራት ፍላጎት አንዳደረበት ጠቅሷል።   በቋሚ ኤግዚቢሽኑ በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የህዋ ቅርጽ ሉላዊ የትዕይንት አዳራሽ ይፋ የተደረገ ሲሆን ስለ-ህዋ ከፍተኛ ጥራት ያላቸው እጅግ አስደማሚ ምስሎችን በማቅረብ የህዋውን አለም እጅግ አቅርቦ ያሳያል።
የበረሃ አንበጣና ፀረ ተባይ መከላከያ ቴክኖሎጂን በስፋት በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ በቅንጅት እየተሰራ ነው - ኮርፖሬሽኑ
Jun 14, 2025 54
አዳማ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ የበረሃ አንበጣና ፀረ ተባይ መከላከያ ቴክኖሎጂን በስፋት በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ ግብርና ስራዎች ኮርፖሬሽን ገለፀ። ኮርፖሬሽኑ ከናሽናል ኤርዌይስና ከሌሎች ባለድርሻዎች ጋር በመሆን በቀጣይ የርጭት አውሮፕላን አገልግሎት ተደራሽነትን ማስፋትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችለውን ውይይት በአዳማ ከተማ አካሂዷል።   የኢትዮጵያ ግብርና ስራዎች ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ ፈለቀ ገዛኸኝ በወቅቱ እንደገለፁት የበረሃ አንበጣን ከመከላከል ባለፈ የሰብል ምርትና ምርታማነትን የሚቀንሱ ተባዮች ለማጥፋት ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ጥቅም ላይ እንዲውሉ እየተደረገ ነው። ኮርፖሬሽኑ የራሱ በሆነ 10ሺህ ሄክታር መሬት ላይ በ22 የሰብል ዓይነቶች ምርጥ ዘር እያባዛ መሆኑን ተናግረዋል። ኮርፖሬሽኑ አሁን ላይ ተጨማሪ 5ሺህ ሄክታር መሬት ወደ እርሻ በማስገባት የተለያዩ የሰብል ምርጥ ዘሮችን በጥራትና በብዛት ለማምረት ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ከናሽናል ኤርዌይስ ጋር በመተባበር በ6ሺህ ሄክታር ላይ የለሙ የተለያዩ የምርጥ ዘር ሰብሎች በአረም፤ በተባይና በሌሎች ተያያዥ የሰብል በሽታዎች እንዳይጎዱ በአውሮፕላን ርጭት መካሄዱን ለአብነት ጠቅሰዋል።   የኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ ምክትል ስራ አስኪያጅ ጫላ አበበ በበኩላቸው ኢንተርፕራይዙ ከ32ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ከ60 በላይ የሰብል ዝርያዎችን በማልማት የምርጥ ዘር ፍላጎትን ለማሟላት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ኢንተርፕራይዙ በ2016/17 ምርት ዘመን ከ800ሺህ ኩንታል በላይ የተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ምርጥ ዘር ማምረቱን ጠቅሰው የፀረ አረምና ፀረ ሰብል በሽታ ማጥፊያ የርጭት አውሮፕላን በመጠቀሙና የሰብል እንክብካቤ ስራ በመስራቱ ከ160ሺህ ኩንታል በላይ ተጨማሪ ምርት ማግኘት መቻሉን አስታውቀዋል። ድርጅቱ በዋናነት በምስራቅ ባሌና ባሌ፣ በአርሲና ምዕራብ አርሲ ዞኖች የስንዴ ልማት እንዲሁም በወለጋ በበቆሎ ምርጥ ዘር ላይ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ኢንተርፕራይዙ በተለይ ከናሽናል ኤርዌይስ ጋር በመተባበር የምርጥ ዘር ብዜት ውጤታማነትን አሁን ካለበት ይበልጥ አጠናክሮ ለማስቀጠል እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። በ2017/18 የምርት ዘመን ከባለድርሻ አካላት ጋር ያለንን ቅንጅት በማጠናከር ምርታማነትን በተሻለ ደረጃ ለማሳደግ አቅደን እየሰራን ነው ሲሉም አክለዋል።   የናሽናል ኤርዌይስ ዋና ስራ አስፈፃሚ ካፒቴን አበራ ለሚ በበኩላቸው ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የበረሃ አንበጣን ጨምሮ የአውሮፕላን ፀረ ተባይና ፀረ መድኃኒቶች ርጭት አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የግብርና ዘርፍ ዕድገት ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የማቅረብ ስራ አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። በቀጣይም በትብብር መስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት ከኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር ተፈራርመዋል።
ለከተማዋ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ባለሙያዎች እያፈራን ነው- ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jun 14, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ለሰው ሃይል ልማት ቅድሚያ ሰጥተን በመስራታችን ለአዲስ አበባ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ ባለሙያዎች እያፈራን እንገኛለን ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናገሩ፡፡ ከንቲባ አዳነች አቤቤ “ብሩህ አዕምሮዎች በክህሎት የበቁ ዜጎች” በሚል መሪ ቃል የሚከበረውን 15ኛውን ከተማ አቀፍ የቴክኒክና ሙያ አውደ ርዕይ መርቀው ከፍተዋል።   አውደ ርዕዩ ከዛሬ ጀምሮ ለአምስት ቀን ክፍት ሆኖ አንደሚቆይ ተገልጿል፡፡ ከንቲባ አዳነች በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ኢትዮጵያ በርካታ የልማት ተግባራትን በማከናወን የብልጽግና መሰረት እየጣለች ትገኛለች፡፡ ኢትዮጵያ የምትበለጽገው የራሳችንን የሰው ሀይልና የተፈጥሮ ሀብት አቀናጅተን በማልማት ነው በሚል ጽኑ አቋም በሰራናቸው ስራዎች የብልጽግና መሰረት እየተጣለ ይገኛል ብለዋል። በዚህም አዲስ አበባን የብልጽግና ማሳያ ለማድረግ የከተማ አስተዳደሩ ቀን ከሌት በትኩረት እየሰራ ይገኛል ነው ያሉት፡፡ እየተከናወኑ ባሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ተግባራት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ከፍተኛ ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ በሰው ሃይል ልማት ላይ በተሰራው ስራ በከተማዋ ልማት አሻራቸውን ያሳረፉ ባለሙያዎችን ማፍራት መቻሉን አንስተዋል፡፡   የቴክኒክና ሙያ ዕውቀትን የቀሰሙ ባለሙያዎች ለከተማዋ ልማት ትልቅ እገዛ የሚያደርጉ የተለያዩ ችግር ፈቺ ማሽኖችን እያመረቱ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡ የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ለኮሪደር ልማቱ ብቁ የሰው ሃይል በማቅረብና የተለያዩ ማሽኖችን በማምረት ያበረከቱትን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ለአብነት አንስተዋል፡፡ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ጥራት ያለው ተኪ ምርት በማምረት ከውጭ የሚገባ ምርትን በማስቀረት ረገድ የራሳቸውን ሚና እየተጫወቱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ከንቲባዋ በዘርፉ የሚነሱ ጥያቄዎችን በመፍታት እና የሚደረገውን ድጋፍ በማጠናከር የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ሚና የበለጠ እንዲጠናከር ይደርጋል ብለዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ስራና ክህሎት ቢሮ ሀላፊ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው ከተማ አስተዳደሩ ባለፉት ሰባት አመታት ከፍተኛ ገንዘብ በመመደብ ተቋማቱን በወርክሾፕ፣ በመሰረተ ልማት፣ በማሽነሪ እና በሰው ሃይል የማጠናከር ስራ ማከናወኑን አስታውቀዋል። በተሰራው ውጤታማ ስራ ኮሌጆቹ ፍላጎት ያላቸው ወጣቶች ሙያ የሚቀስሙባቸው ተቋማት ለመሆን መብቃታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ አውደ ርዕዩ ህብረተሰቡ በዘርፉ የተፈጠረውን አቅም እንዲገነዘብ ለማድረግ የተዘጋጀ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በአውደ ርዕዩ ከ150 በላይ የፈጠራ ውጤቶች ለእይታ የሚቀርቡ ሲሆን የፓናል ውይይቶችና ሌሎች መርኃ ግብሮች እንደሚካሄዱ ተመላክቷል።
ቋሚ ኤግዚቢሽኑ የነገዋን ኢትዮጵያ የምንሰራበት ትልቅ ሀብት የያዘ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jun 14, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽን የነገዋን ኢትዮጵያ የምንሰራበት እና የምንገነባበት ትልቅ ሀብት የያዘ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ኤግዚቢሽኑ ልጆች የነገ ማንነታቸው እንዲሰራ እና የነገ መሻታቸው እውን እንዲሆን የሚያደርግ ነውም ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽን ክፍል ዛሬ በይፋ ተከፍቷል።   ኤግዚቢሽኑ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና የኢትዮጵያ ምላሽ፣ ግብርና፣ የውኃ ኃይል እና ኢነርጂ፣ ኤሮኖቲክስ እና አቪየሽን ላይ ያተኮሩ አምስት የዐውደ ርዕይ ምድቦችን የያዘ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሳይንስ ሙዚየም ሕንጻ ከሁለት ዓመት ገደማ በፊት ተገንብቶ በጊዜያዊ ኤግዚቢሽን መመረቁን አስታውሰዋል። ቋሚ ኤግዚቢሽኑ ከፍተኛ ሀብት መጠየቁን ጠቁመው በጣም ጠቃሚ ነገር የያዘ መሆኑንና ነገን የምንሰራበት ሙዚየም እዚህ ነው ያለው ሲሉ ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያን ነገን መስራት ነገን መለወጥ ከፈለጉ ልጆቻቸውን ወደ ኤግዚቢሽኑ ስፍራ ሊያመጧቸው እንደሚገባም አመልክተዋል።   ልጆች በሙዚየሙ ያሉ ነገሮችን በተግባር በማየት የነገ ማንነታቸውን መስራት እና የነገ መሻታቸውን እውን ማድረግ ይችላሉ ሲሉም ገልጸዋል። ኤግዝቢሽኑ ለልጆች ታላቅ በረከት ይዞ መጥቷል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጆች ቴክኖሎጂን በሚገባ እንዲጠቀስሙ እና አልፎም ፈጣሪ እንዲሆኑ በር የሚከፍት ነው ብለዋል። ወላጆች ቋሚ ኤግዚቢሽኑ ለልጆች ትልቅ ዕድል መሆኑን ተገንዝበው ወደ ስፍራው ይዘዋቸው እንዲመጡ እና መልካም ዘርን እንዲዘሩባቸው አስገንዝበዋል። ይህንን እያየ ያደገ ልጅ ጥበብ እና እውቀትን በማዳበር ነገ ሀገሩን የሚጠብቅ፣ ሀገር የሚያበለጽግ፣ ሀገር የሚያለማ እና ሀገር የሚያጸና ይሆናል ሲሉም ተናግረዋል። በተጨማሪም መምህራን፣ ተመራማሪዎችና ነገን መስራት የሚፈልጉ ሰዎች በሙሉ ኤግዚቢሽኑን እንዲጎበኙ ጥሪ አስተላልፈዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለቋሚ ኤግዚቢሽኑ ግንባታ ድጋፍ ላደረጉ ሀገራት እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ምስጋና አቅርበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽን ክፍል በይፋ ተከፈተ
Jun 14, 2025 45
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት የሳይንስ ሙዚየም ቋሚ ኤግዚቢሽን ክፍል በይፋ ተከፍቷል። ይኽ ድንቅ ክንውን በአርቴፊሻል ኢንተሊጀንስ፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና የኢትዮጵያ ምላሽ፣ ግብርና፣ የውኃ ኃይል እና ኢነርጂ፣ ኤሮኖቲክስ እና አቪየሽን ላይ ያተኮሩ አምስት የዐውደ ርዕይ ምድቦችን የያዘ ነው።   ይኽም ሀገራችን ሳይንስ እና ቴክኖሎጂን ለመጠቀም ያላትን ጽኑ ፍላጎት የሚያሳይ ነው ሲል የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። በተጨማሪም በሀገራችን የመጀመሪያ የሆነው የህዋ ቅርጽ ሉላዊ የትእይንት አዳራሽም ይፋ ሆኗል። በ1000 ሜትር ስኩዌር ሜትር እና 36 ሜትር ዲያሜትር ይዞ ያረፈው አዳራሽ ዘመኑን በዋጀ የ4k ዲጂታል ምስል ማሳያ ቴክኖሎጂ የተገጠመለት መሆኑንም ገልጿል።   ምስለ-ህዋው ከፍተኛ ጥራት ያለው እጅግ አስደማሚ ምስሎችን በማቅረብ የህዋውን አለም እጅግ አቅርቦ ያሳያል። እውቀት ለማሰስ፣ ለመማር እና ለመነሳሳት ምቹ የሆነው የሳይንስ ሙዚየም ለጎብኚዎች ክፍት መሆኑንም አስታውቋል። ህዝቡም መጥቶ የኢትዮጵያን የሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መፃዒ ተስፋ እንዲመለከቱ ጽህፈት ቤቱ ጋብዟል።
የህግ ታራሚዎች ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይበልጥ ማሳደግ ይገባል
Jun 13, 2025 54
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ የህግ ታራሚዎች ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚገባ የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ቴዎድሮስ ምህረት ተናገሩ። የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ከፌደራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ጋር በመተባበር በኮሚሽኑ ከፍተኛ ጥበቃ ማረሚያ ማዕከል ለህግ ታራሚዎች አገልግሎት የሚውል የፕላዝማ ችሎት አገልግሎትና የኢ-ፋይሊንግ ሥርዓትን አበልፅጎ ወደ ስራ አስገብቷል።   የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ቴዎድሮስ ምህረት በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ማረሚያ ቤቶች የፍርድ ቤቶችን ውሳኔ የሚያስፈጽሙ በመሆናቸው ህገ-መንግስቱን፣ የኢትዮጵያንና የዓለም አቀፍ ህጎችን ባከበረ መልኩ ታራሚዎችን መያዝ ይገባቸዋል፡፡ በዚህም የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ከፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ጋር በመተባበር የፕላዝማ ችሎት እና ኢ-ፋይሊንግ ሲስተም አበልፅጎ ወደ ስራ አስገብቷል ነው ያሉት። የቀጠሮ ምልልስ፣ እንግልት እና ጊዜን በአግባቡ ለመጠቀም ይህን ፕሮጀክት ወደ ስራ ማስገባት አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱን አንስተዋል። ተቋማትን በቴክኖሎጂ በማዘመን የታራሚዎችን የፍትህ ጥያቄ በፍጥነት መመለስ እንደሚያስችል ገልጸው፤ የህግ ታራሚዎች ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይበልጥ ማሳደግ ይገባል ብለዋል።   የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጄኔራል የኑስ ሙሉ በበኩላቸው መንግስት ባስቀመጠው የሪፎርም አቅጣጫ መሠረት ማረሚያ ቤቶች ዜጎች ታርመውና ታንፀው አምራችና ህግ አክባሪ ሆነው ወደ ሠላማዊ ህይወት እንዲመለሱ አበረታች ተግባር መከናወኑን ተናግረዋል። ለአገልግሎት ክፍት የተደረገው የፕላዝማ ችሎት አገልግሎት እና ኢ-ፋይሊንግ ሲስተም አንዱ ማሳያ መሆኑን በመጠቆም። የሪፎርም ዕቅዱ ካስቀመጣቸው የትኩረት አቅጣጫዎች መካከል የህግ ታራሚዎችን የሰብዓዊ መብት አያያዝ ማሻሻል ነው ብለዋል። የተጀመሩ የለውጥ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ኮሚሽነር ጄኔራሉ አረጋግጠዋል።      
የሳይበር ጥቃቶችን ለመቋቋም የሳይበር ደህንነት ላይ የሚሰሩ ምርምሮችን መደገፍ ያስፈልጋል - ሚኒስቴሩ
Jun 13, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ በየጊዜው የሚቀያየረውን የሳይበር ጥቃት ለመቋቋም የሳይበር ደህንነት ላይ የሚሰሩ ምርምሮችን መደገፍ እንደሚያስፈልግ የኢኖቬሸንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ገለጸ። የኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ማህበር በሳይበር ደህንነት ላይ ትኩረት ያደረገ “ዓለም አቀፍ የሳይበር ደህንነት እና ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን በኢትዮጵያ" በሚል ሀሳብ ጉባዔ እያካሄደ ይገኛል።   የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ፎዚያ አሚን(ዶ/ር) በጉባዔው መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት፤ የሳይበር ደህንነትን ለማስጠበቅ የፈጠራ ስራዎች ወሳኝ ናቸው። ይህንንም ውጤታማ ለማድረግ የሳይበር ደህንነት ላይ የሚከናወኑ ምርምሮችን መደገፍ አስፈላጊ ነው ብለዋል። የሳይበር ደህንነት መሪ በሚሆነው ትውልድ ላይ መስራት እንደሚገባ ገልጸው፤ የሳይበር ደህንነት ላይ የሚሰሩ ምርምሮችን በማጠናከርና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተደራሽ በማድረግ በዘርፉ አዎንታዊ ሚና መጫወት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። ከምሁራን፣ ከሲቪክ ማህበራትና ዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል። የሳይበር ደህንነት የማስጠበቅ ስራን ስኬታማ ለማድረግ ትብብር ወሳኝ መሆኑን አመላክተው፤ በዘርፉ ያለውን እውቀት፣ መልካም ተሞክሮና ሀብት በመጠቀም በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል። የሳይበር ደህንነት ተግዳሮቶችን ለማስወገድና የጋራ መፍትሄዎችን ለመፍጠር ከአጋር አካላት ጋር የሚሰሩ ስራዎችን እንደሚጠናከሩም ተናግረዋል። ጉባዔው የዲጂታል ዘርፉን ቀጣይ ምዕራፍ የሚያመላክት እና የዲጂታል ሽግግሩን ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ ግብዓት ለመሰብሰብ ያግዛል ነው ያሉት።   የዓለም አቀፍ የቴሌኮሙኒኬሽን ሕብረት የአፍሪካ ቀጣናዊ ዳይሬክተር ኢማኑኤል ማናሳህ እንዳሉት የዲጂታል ሽግግር ስራዎችን ለማጠናከር ትስስር መፍጠር፣ የዲጂታል ክህሎትና የፈጠራ ችሎታን ማዳበር ያስፈልጋል። የሳይበር ደህንነትን ማስጠበቅ፣ መዋዕለ ነዋይን ማፍሰስ፣ ህግና ፖሊሲዎችን ማሻሻል እንዲሁም ምቹ ከባቢ መፍጠር ወሳኝ መሆኑን አክለዋል። አፍሪካውያን በትብብር በመስራት ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ተመጣጣኝና ቀልጣፋ የዲጂታል አገልግሎት እንዲጠናከር ማድረግ አለባቸው ብለዋል።   የኢትዮጵያ የሳይበር ደህንነት ማህበር ፕሬዝዳንት ብርሃኑ በየነ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የሳይበር ደህንነት ስጋቶች ውስብስብና በየጊዜው ተለዋዋጭ በመሆናቸው አፍሪካውያን በጋራ መስራት ይኖርባቸዋል ብለዋል። ይህም ዲጂታል እሴቶችን እና መሰረተ ልማቶችን መጠበቅ እንደሚያስችል ተናግረዋል። ኮንፍረንሱ በሀገር እና በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚገኙ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ አካላት፣ ተመራማሪዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የሀሳብና የልምድ ልውውጥ ለማድረግና በጋራ እንዲሰሩ እድል ይፈጥራል ብለዋል።
በበጀት አመቱ በአገር-አቀፍ ደረጃ ተፈጻሚ የሚሆኑ 18 አስገዳጅ ደረጃዎች ጸድቀው ወደ ስራ ገብተዋል
Jun 11, 2025 193
አዲስ አበባ፤ሰኔ 4/2017(ኢዜአ)፦ በ2017 በጀት አመት በአገር-አቀፍ ደረጃ ተፈጻሚ የሚሆኑ 18 አስገዳጅ ደረጃዎች ጸድቀው ወደ ስራ መግባታቸውን የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲቱዩት ዋና ዳይሬክተር መሰረት በቀለ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር መሰረት በቀለ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩቱት ስራ ከጀመረ ከ50 አመት በላይ ማስቆጠሩን ተናግረዋል፡፡ በእነዚህ አመታት አለም አቀፍ አሰራርን ተከትሎ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ ለተለያዩ ምርቶችና አገልግሎቶች ብሔራዊ የጥራት ደረጃዎችን ሲያዘጋጅ መቆየቱን ተናግረዋል፡፡ እስካሁን ድረስም ከ12 ሺህ በላይ ብሔራዊ የጥራት ደረጃዎችን አዘጋጅቶ ስራ ላይ እንዲውሉ ማድረግ መቻሉን ነው የተናገሩት፡፡ ከነዚህ ደረጃዎች ውስጥ 414 የሚሆኑት የምርትና የአገልግሎት አይነቶች አስገዳጅ ደረጃዎች መሆናቸውን አመላክተዋል፡፡ በሰው ህይወት፣በእንስሳት፣ በእጽዋት፣በአካባቢ እና በብሔራዊ ደህንነት ላይ አደጋ የሚያስከትሉ ምርትና አገልግሎቶች አስገዳጅ ደረጃ እንደሚወጣላቸው ጠቁመዋል፡፡ በ2017 በጀት አመት በአገር አቀፍ ደረጃ ተፈጻሚ የሚሆኑ 18 አስገዳጅ ደረጃዎች ጸድቀው ወደ ስራ መግባታቸውን ተናግረዋል፡፡ ኢንስቲቱዩቱ በምርት ጥራት መጓደል የሚከሰቱ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመከላከል በወጪ፣በገቢ እና በአገር ውስጥ ጥቅም ላይ በሚውሉ ምርቶች ላይ የሚለጠፉ የጥራት ደረጃ ምልክቶችን አዘጋጅቶ ወደ ስራ ማስገባቱን ተናግረዋል፡፡ ለተግባራዊነቱም ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የጥራት ምልክቶቹ ተመሳስለው የሚመረቱ ህገ-ወጥ ምርቶችን ከትክክለኛው ምርት ለመለየት የሚያስችሉ ናቸው ብለዋል፡፡ አምራቾች በሚያመርቷቸው ምርቶች ላይ የጥራት ደረጃ ምልክቶችን መጠቀም እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡
በኢትዮጵያ 155ሺህ ስደተኞችን የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ማድረግ ተችሏል - የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት
Jun 10, 2025 433
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ 155ሺህ ዓለም አቀፍ ስደተኞችን የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት በማድረግ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎት እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ጠይባ ሐሰን አስታወቁ። የኢትዮጵያ ስደተኞችን የመቀበል ታሪክ ከህዝቦቿ የእንግዳ ተቀባይነት ባህል የሚመነጭ ነው ብለዋል። ከጎረቤት ሀገራት የመጡ ስደተኞችም ከተቀባዩ ማህበረሰብ ጋር ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስተጋብርን በሚያሳድጉ መስኮች በመሳተፍ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን በማጠናከር ዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነትን እያጎለበተ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ለአብነትም ከጎረቤት ሀገር ደቡብ ሱዳን፣ ከሱዳንና የመሳሰሉት ሀገራት የሚመጡ ስደተኞች የኢትዮጵያ አምባሳደር በመሆን ጭምር ልዩ ክብር እንዳላቸው ተናግረዋል። በቆይታቸውም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚያገኙት ዕውቀትና ክህሎትም ወደ ሀገራቸው ሲመለሱ ኢትዮጵያን እንደሁለተኛ ሀገራችው እንደሚቆጥሯት ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋን በመሸሽ ጎረቤት ሀገራትን ጨምሮ ከ34 ሀገራት በላይ የመጡ ከ1 ነጥብ 1 ሚሊየን በላይ ስደተኞች በኢትዮጵያ እንደሚኖሩ ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥ ከደቡብ ሱዳን፣ ከሱዳን፣ ከኤርትራና ከሱማሊያ የመጡ ስደተኞች ትልቁን ቁጥር በመያዝ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ብዙ ቁጥር ያለው ዓለም አቀፍ ስደተኛ የምታስተናግድ ሀገር እንድትሆን እንዳስቻላት አስታውቀዋል። ስደተኞች የዲጂታል መታዊቂያ ባለቤት እንዲሆኑ ለማድረግም በብሔራዊ መታወቂያ መርሃ ግብር፣ በገንዘብ ሚኒስቴርና በአገልግሎቱ ትብብር እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በአጭር ጊዜ ውስጥም በኢትዮጵያ ከሚኖሩ ስደተኞች መካከል 155ሺህ ስደተኞችን የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት በማድረግ በኢትዮጵያ የሚሰጡ አገልግሎቶችን በቀላሉ እንዲያገኙ እየተደረገ ነው ብለዋል። የዲጂታል መታወቂያው ስደተኞች ከዚህ ቀደም የሚያጋጥማቸውን የአገልግሎት መስተጓጎል በማስቀረት ከፍተኛ ጠቀሜታ እያበረከተላቸው እንደሚገኝ አንስተዋል። ኢትዮጵያ ስደተኞችን በመቀበል የምታስተናግደበት አሰራር በዓለም አቀፍ ደረጃ ዲፕሎማሲያዊ ትብብርን ማሻሻል ያስቻለ ምስጋና እየተቸራት መሆኑንም አንስተዋል። ዓለም አቀፍ ረጂ ድርጅቶች በሚቀርጿቸው ፕሮጀክቶች ስደተኞችንና ተቀባዩን ማህበረሰብ ተጠቃሚ በሚያደርጉ የልማት ሰራዎች ላይ እንዲውል እየተደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዓለም አቀፍ አሰራር መሰረት ስደተኛ ተቀባይ መንግስታት ተገን በመስጠትና ደኅንነትን እንደሚጠብቁ ጠቅሰው፤ ረጂ ድርጅቶችና ለጋሽ አካላትም መሰረታዊ ድጋፎችን እንዲሚያቀርቡ አስረድተዋል። ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በኢትዮጵያ ለሚገኙ ስደተኞች የሚቀርቡ የጤና፣ የምግብና ትምህርትን ጨምሮ ሰብዓዊና መሰረታዊ ድጋፎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እያቆሙ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም ጫና መፍጠሩን አንስተዋል። በዚህም ዓለም አቀፍ ረጂ ድርጅቶችና ለጋሽ አካላት በኢትዮጵያ ለሚገኙ ስደተኞች የሚያቀርቡትን የተለያዩ ድጋፎች አጠናክረው እንዲቀጥሉ ዋና ዳይሬክተሯ ጥሪ አቅርበዋል።
በኢትዮጵያ የኒውክሌር ቴክኖሎጂን ለጤና፣ለግብርናና ለኃይል አቅርቦት ዘርፎች መጠቀም የሚያስችል ጥናትና ምርምር እየተደረገ ነው
Jun 7, 2025 287
አዲስ አበባ፤ግንቦት 30/2017(ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካ ኒውክሌር ሳይንስና ቴክኖሎጂ ማዕከል ሆኖ መመረጡ ይታወቃል። በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ማዕከል ኃላፊ ደረጃው አየለ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፥ዩኒቨርሲቲው ከኒውክሌር ኢነርጂ ሰላማዊ የኃይል አማራጭ ተጠቃሚ የሚያደርጋትን የልህቀት ማዕከላት ገንብቷል፡፡ ዩኒቨርሲቲው የአፍሪካ የኒውክሌር ሳይንስ ማዕከል ሆኖ መመረጡ በዘርፉ ስኬታማ የጥናትና ምርምር ስራዎችን ለመሥራት ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል። በማዕከሉ በተለያዩ የምርምር መስኮች ላይ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በመተባበር ትልልቅ የጥናትና ምርምር ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን አስታውቀዋል። በቀጣይም በኒውክሌር ቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎትን ካካበቱ የሩሲያ፣ ኮሪያና ቻይና ተመራማሪና የልህቀት ማዕከላት ጋር ጠንካራ ትብብር በመፍጠር እንደሚሰራ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የኒውክሌር ቴክኖሎጂን ለጤና፣ለግብርናና ለኃይል አቅርቦት ዘርፎች መጠቀም የሚያስችል ጥናትና ምርምር እየተካሄደ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በዩኒቨርስቲው የ2ተኛ ዓመት የኒውክሌር ሳይንስ ኢንጂነርንግ ተማሪ ቴዎድሮስ አበባው፥ በዩኒቨርሲቲው የኒውክሌር ትምህርት መሰጠቱ ኢትዮጵያን በዘርፉ ተጠቃሚ የሚያደርግ ዕውቀትና ክህሎት ያለው ዜጋ ለማፍራት ትልቅ ዕድል መፍጠሩን ገልጿል። የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካ የኒውክሌር ሳይንስና ቴክኖሎጂ ማዕከል ሆኖ የተመረጠ ሲሆን በማስተርስ ዲግሪ ተማሪዎችን ተቀብሎ በማስተማር ላይ ይገኛል። በሚያዝያ ወር መጨረሻ የዓለም አቀፍ አቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲና የቻይናው ሽንግዋ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር፣በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ሥር የአፍሪካ ኒውክሌር ሳይንስ ማዕከል እንዲቋቋም ስምምነት ማድረጋቸው ይታወቃል።
ኢትዮጵያና ስሎቪኒያ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስና ህዋ ሳይንስ በትብብር እንደሚሰሩ ገለጹ
Jun 5, 2025 193
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያና ስሎቪኒያ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስና በህዋ ሳይንስ በትብብር እንደሚሰሩ ገለጹ። የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ የስሎቪኒያ ፕሬዚዳንት ናታሻ ፒርክ ሙሳርን በብሔራዊ ቤተመንግስት ተቀብለው አነጋግረዋል። ፕሬዚዳንት ታዬ ከውይይቱ በኋላ ለጋዜጠኞች በሰጡት ማብራሪያ ከስሎቪኒያ ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት ጋር በዓለም አቀፍና የሁለትዮሽ ጉዳዮች ላይ መምከራቸውን ገልጸዋል። ስሎቪኒያ የተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት ተለዋጭ አባል በመሆኗ በቆይታዋ፣ ምክር ቤቱ የአፍሪካ ጉዳዮችን በሚያይበት ወቅት ማገዝ በምትችልባቸው ጉዳዮች ላይ መወያየታቸውን ገልጸዋል። አፍሪካን በሚመለከት ሚዛናዊ እይታ ያላቸው፣ የአፍሪካ ድምጽ በመታበይ ስሜት ሳይሆን እኩልነትና ሚዛናዊነትን የሚፈልጉ እንደሆኑ መረዳታቸውን አንስተዋል። የጸጥታው ምክር ቤት በጂኦ-ፖለቲካልና ጂኦ-ኢኮኖሚክ መስፈርቶችና የአገራት ብሔራዊ ጥቅምን ማዕከል በማድረግ ሪፎርም ለማድረግ መሰራት ባለባቸው ጉዳዮች ዙሪያም መወያየታቸውን ተናግረዋል። ዓለም አቀፍ ውጥረት የባለብዙወገን ሃሳብና ዲፕሎማሲ ፈተና ውስጥ ከወደቀባቸው ቁልፍ ጉዳዮች አንዱ እንደሆነ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ጠቁመዋል። ጥቂት ሀገራት በአለም ህልውና ላይ ሊወስኑ እንደማይገባ በመግለጽ በመካከለኛ ሃይል ሊፈረጁ የሚችሉ ሀገራት ሊኖራቸው በሚችለው ድምጽ ላይ መክረናል ብለዋል። በሁለትዮሽ ጉዳዮች ስሎቪኒያ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስና በስፔስ ሳይንስ ያላትን የዳበረ አቅም በማሸጋገር ዙሪያ በጋራ ለመስራት በአጽእኖት መወያየታቸውን ገልጸዋል። በምግብ ራስን ለመቻል በከተማ ግብርና በንብ ማነብ ያላቸውን ልምድ በማካፈል በትብብር እንደሚሰሩም አብራርተዋል። የስሎቪኒያ ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት ናታሻ ፒርክ ሙሳር በበኩላቸው፤ ከኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ጋር በሁለትዮሽ፣ በአለም አቀፍና የባለብዙ ወገን ግንኙነት ላይ ውጤታማ ውይይት ማድረጋቸውን ተናግረዋል። አፍሪካ በጸጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዲኖራት ስሎቪኒያ ሙሉ ድጋፍ እንደምታደርግም ገልጸዋል። ከኢትዮጵያ ጋር በምጣኔ ሃብት፣ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የውሃ አስተዳደርና በሌሎች ዘርፎች በትብብር መስራት የሚፈልጉባቸው እንደሆኑ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ልዩ መለያ የሆኑ የግብርናና የዕደ-ጥበብ ፈጠራ ውጤቶች የባለቤትነት መብት መረጋገጥ ለዘርፉ ዕድገት ጉልህ ሚና ይኖረዋል
Jun 5, 2025 139
አዲስ አበባ፤ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ልዩ መለያ የሆኑ የግብርናና የዕደ ጥበብ ፈጠራ ውጤቶች የባለቤትነት መብት መረጋገጥ ለዘርፉ ዕድገት ጉልህ ሚና እንደሚኖረው አምራቾች ገለጹ። ኢትዮጵያ ቡናን ጨምሮ ልዩ ጣዕምና ባህሪ ያላቸው የግብርና ምርቶችን በስፋት የምታበቅል መሆኗ ይታወቃል። በተለያዩ አካባቢዎች የሚመረቱ የእጅ ጥበብና የግብርና ምርቶችም በልዩ ባህሪያቸው በቀላሉ ይለያሉ። እነዚህ ምርቶች ተገቢውን ዕውቅና አግኝተው አምራቹን ተጠቃሚ እንዲያደርጉና አገሪቷን በሚገባው ልክ እንዲያስተዋውቁ ብዙ ስራ መስራትን ይጠይቃል። የባህል አልባሳት አምራች ወንድወሰን ይርጋለም፥ የባህል አልባሳት የኢትዮጵያ ልዩ መለያ በመሆናቸው የእጅ ጥበቡን ጠብቆ ለትውልድ ማስተላለፍ ይገባል ብሏል። በባህል አልባሳት ዲዛይን ላይ የሚደረጉ ፈጠራዎች ተገቢውን የባለቤትነት ዕውቅና ቢያገኙ ለፈጠራው ባለቤትም ሆነ ለሌሎች አምራቾች መነሳሳትን እንደሚፈጥር ተናግሯል።   በሸክላ ስራ ላይ የተሰማሩት መዓዛ አሰግድና በእጅ ጥበብ ሥራ የተሰማሩት ትዝታ ሞረዳ በቡላቸው፣የእጅ ጥበብ ውጤቶቹ የተለያየ ፈጠራ ታክሎባቸው የኢትዮጵያን ባህል በሚያስተዋውቅ መልኩ እንደሚሰሩ ገልጸዋል። የዕደ ጥበብ ውጤቶች እንደአካባቢው የተፈጥሮ ሃብትና የህብረተሰቡ የአኗኗር ዘይቤ የሚለያዩ ቢሆንም የኢትዮጵያን ብዝሃነትና ቱባ ባህል በማሳየት ረገድ ፋይዳቸው የጎላ መሆኑንም ነው ያነሱት። ከትውልድ ትውልድ ሲተላለፍ የቆየውን የዕደ ጥበብ ውጤት ጠብቆ ለማቆየት ለባለሙያዎቹ ተገቢው የፈጠራ ባለቤትነት መብት ሊሰጥ እንደሚገባ ተናግረዋል።   የጋሞ ገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበር አትክልትና ፍራፍሬ አምራች ሲሳይ ቦጋለ በበኩላቸው፣ በአካባቢያቸው የሚበቅሉት የተለየ ጣዕም ያላቸው የፍራፍሬ ምርቶች በተጠቃሚዎች ዘንድ ተወዳጅ መሆናቸውን ያነሳሉ። ማንጎና ሙዝን ጨምሮ እነዚህ ልዩ ጣዕምና ዕውቅና ያላቸው ምርቶች ጥራትና ተወዳጅነታቸውን ጠብቀው እንዲቆዩ እውቅና መሰጠቱ አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ሰርተፊኬሽን ማዕከል የቡና ከፍተኛ ጣዕም መርማሪ ግሩም መኮንን፣ኢትዮጵያ የተለያየ ጣዕም ያላቸው የቡና ዝርያዎች የሚመረቱባት አገር መሆኗን ያነሳሉ።   እነዚህ የቡና ዝርያዎች ከሚመጡበት አካባቢ ስያሜ እንደሚያገኙና የታጠቡና ያልታጠቡ ተብለው እንደሚለዩ አመልክተዋል። ቡናዎች እንደየመጡበት አካባቢ የጥራት ደረጃቸውን ጠብቀው ተወዳዳሪ ዋጋ እንዲያገኙ ለአምራቹ ተገቢው ዕውቅና ሊሰጥ ይገባል ብለዋል። በአለም አቀፍም ሆነ በአገር ደረጃ ልዩ ጣዕም ያላቸውን ቡናዎች ጥራትና ተወዳዳሪነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል በበኩላቸው፥ የኢትዮጵያ ልዩ ባህሪ ያላቸው ምርቶችና የዕደ-ጥበብ ውጤቶችን የፈጠራ ባለቤትነትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎች መጀመራቸውን ገልጸዋል።   በተለይም ምርቶቹ በመልክዓ ምድራዊ አቀማመጥና በልዩ ባህሪያቸው ተለይተው ለገበያ እንዲቀርቡ የሚያስችሉ ሰነዶች እየተዘጋጁ መሆኑንም ነው የተናገሩት። ምርቶቹ በተመረቱበት አካባቢ ባሉ የህብረት ስራ ማህበራት የጥራት ደረጃቸው ተመዝግቦ የማረጋገጫ ሰርተፊኬት እንዲሰጣቸው ይደረጋል ብለዋል። ይህም ምርቶች እንዳይደበላለቁ እንዲሁም ለፈጠራ ባለቤቶች ዕውቅና ለመስጠት ያስችላል ብለዋል።
የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ የኮደርስ ስልጠናን እንዲወስዱ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ ነው - የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ
Jun 5, 2025 133
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦ የዩኒቨርሲቲው ማህበረሰብ የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ስልጠናን እንዲወስዱ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ መሆኑን የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ገለፀ። የ“አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ’’ መርኃ ግብር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ይፋ የተደረገ ሲሆን በኢትዮጵያ እና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መንግሥታት ትብብር እየተተገበረ ይገኛል። ፕሮጀክቱ "ትውልድ ይማር፣ ትውልድ ይሰልጥን፣ ከዓለም ጋር ይፎካከር" በሚል እሳቤ ወጣቶች የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማዳበር በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እና ብቁ ማድረግ የሚያስችል ነው። መርኃ ግብሩ በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት የሚያስጨብጥ ነው።   የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የኤሌክትሮኒክስ ትምህርት ክፍል ዳይሬክተር መኮንን አበበ(ዶ/ር) የአምስት ሚሊየን ኮደርስ መርኃ ግብር ዜጎችን ከአለም ቴክኖሎጂ ጋር የሚያስተሳስር ነው ብለዋል። የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች እና ማህበረሰብ ስልጠናውን እንዲከታተሉ ለማድረግ ሲሰራ መቆየቱን አስታውሰው በዚህም ስልጠናውን የተከታተሉ ተማሪዎችና ሰራተኞች ቁጥር ከ2ሺህ 800 መሻገሩን ተናግረዋል። እስካሁን ባለው ሂደት 68 መምህራንና ከ730 በላይ የአስተዳደር ሰራተኞች ስልጠናውን ማጠናቀቃቸውንም ጠቅሰዋል። የኮደርስ ስልጠና የተማሪዎችን የዲጂታል ክህሎት የሚያሳድግ መሆኑን ተከትሎ ስልጠናውን በስፋት እንዲወስዱ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም 1ሺህ 80 የመጀመሪያ አመት እንዲሁም ከሁለተኛ አመት በላይ ያሉ 983 ተማሪዎች ስልጠናውን ማጠናቀቃቸውን አብራርተዋል። የኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ክህሎትንና ተወዳዳሪነትን የሚያሳድግ በመሆኑ ሁሉም ስልጠናውን ቢከታተል ተጠቃሚ እንደሚሆንም አስገንዝበዋል።   በዩኒቨርሲቲው የኤሌክትሪካልና ኮምፒውተር ምህንድስና ተማሪ ሰለሞን ታረቀኝ የኮደርስ ስልጠና ለትምህርቱ እገዛ እንደሚያደርግለት ገልጿል።   ሌላው የኤሌክትሪካልና ኮምፒውተር ምህንድስና ተማሪ ቅዱስ ማሞ የኮደርስ ስልጠናን መውሰዱ በተለይ የጥናት ስራን ለማካሄድ እንደሚጠቅመው ተናግሯል። ስልጠናው የዲጂታል ክህሎትን የሚያሳድግ በመሆኑ ሁሉም ተማሪ የተመቻቸውን ዕድል በመጠቀም ሊከታተለው እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት።
በከተማዋ ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት 278 አገልግሎቶች በበይነ መረብ እንዲሰጡ ተደርጓል - ቢሮው
Jun 5, 2025 94
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት 278 አገልግሎቶች በበይነ መረብ እንዲሰጡ ማድረግ መቻሉን የአዲስ አበባ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ እና የመዲናዋ ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን አገልግሎትን ማዘመን የሚያስችለውን የስማርት ኦፊስ ስራ ሰኔ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ወደ ስራ እንደሚያስገባ አስታውቋል። የቢሮው ኃላፊ አዋሌ መሀመድ ለኢዜአ እንዳሉት በስማርት ሲቲ ትግበራ አዲስ አበባን ለነዋሪዎቿ ምቹና ዘመናዊ ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። በስማርት ሲቲ ትግበራ አገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ ማስደገፍ መቻሉ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ብለዋል። በሲቲ ኔት የዲጂታል መሰረተ ልማት ፕሮጀክት 58 ተቋማት፣ 11ዱ ክፍለ ከተሞችና ሁሉም ወረዳዎች እንዲተሳሰሩ መደረጉንም ተናግረዋል። በከተማዋ 582 አገልግሎቶችን በበይነ መረብ ለመስጠት መለየቱን ተናግረው ከእነዚህ መካከል 278 አገልግሎቶች በበይነ መረብ እንዲሰጡ ማድረግ መቻሉንም ገልፀዋል። ህብረተሰቡ ጥያቄ የሚያነሳባቸውን አገልግሎቶች በመለየትና ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት በበይነ መረብ እንዲተገበሩ መደረጋቸውን አንስተዋል። ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ ማድረግ የሚያስችሉ የስማርት አገልግሎቶችን የማስፋት ስራ ተጠናክሮ እንደቀጠለም አስረድተዋል። በአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ እና ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን የስማርት ኦፊስ ስራ በማከናወን አገልግሎት አሰጣጡን የማዘመን ስራ መከናወኑንና ሰኔ 1 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚመረቅ ገልፀዋል። የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቶማስ ደበሌ ሁለቱ ተቋማት የሚሰጡትን አገልግሎት ለማዘመን የሪፎርም ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ስማርት ኦፊስ ለመገንባት የተለያዩ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቁመው ከጨረታ ጀምሮ እስከ ቤት ማስተላለፍ ያለውን ሂደት የማዘመን ስራ መሰራቱን ጠቁመዋል። በተቋማቱ ከፍተኛ አቅም ያለው የዳታ ማዕከል፣ የሶፍትዌር ልማት፣ ዘመናዊ የጂም ግንባታና ሌሎች አገልግሎቶችን የማዘመን ስራ መሰራቱን ጠቅሰዋል። በተዘረጉት አዳዲስ መሰረተ ልማቶችና በለሙ ሶፍትዌሮች ላይ ሙከራ መደረጉንና ከደህንነት ጋር የተያያዘ ፍተሻ በማከናወን አስተማማኝነታቸውን ማረጋገጥ መቻሉን አስታውቀዋል።
በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የተያዘውን ራዕይ እውን ለማድረግ በተከናወኑ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ነው - ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር)
Jun 4, 2025 93
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2017(ኢዜአ)፦ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የተያዘውን ራዕይ እውን ለማድረግ በተከናወኑ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ባለስልጣን በጥራት መንደር ውስጥ የተረከበውን ህንጻ ምርቃት መርሃ ግብር አካሂዷል።   በመድረኩ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር)፣ የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ(ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሰለሞን ጌታቸው እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የተያዘውን ራዕይ እውን ለማድረግ በተከናወኑ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ነው።   የጥራት መንደሩ ለኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑን አንስተው፤ መንደሩ ለኢኮኖሚ ዕድገት ወሳኝ የሆኑ ተቋማት በቅንጅት የሚሰሩበት መሆኑን ጠቁመዋል። ይህም ኢትዮጵያን በአፍሪካ በጉልህ የሚያስቀምጣት መሰረተ ልማት መሆኑን ተናግረዋል።   የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ(ዶ/ር) የኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ባለስልጣን በጥራት መንደር እንዲገቡ ከተፈለጉ ተቋማት መካከል አንዱ መሆኑን ገልጸዋል። የጥራት መንደር የኢትዮጵያን የልማት መሻት የዋጀ የነገ ፍላጎታችንም ማሳያ እንዲሁም ለትውልድ የሚተርፍ ጸጋ መሆኑን ገልጸዋል። የባለስልጣኑ ሰራተኞች በግቢው ያሉ መሰረተ ልማቶች እንዲጠበቁ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡም አሳስበዋል።   የኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሰለሞን ጌታቸው የተረከቡት ህንጻ ባለስልጣኑ የተሰጠውን ተልዕኮ በአግባቡ መወጣት የሚያስችለው መሆኑን ተናግረዋል።
ዲጂታል የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት የአሠራር ሥርዓት መዘርጋቱ ቀልጣፋና ጥራት ያለው አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል - ተገልጋዮች
Jun 4, 2025 90
አዲስ አበባ፤ግንቦት 27/2017(ኢዜአ)፦ዲጂታል የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት የአሠራር ሥርዓት መዘርጋቱ ቀልጣፋና ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኙ እንዳስቻላቸው ተገልጋዮች ገለጹ። የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ በቴክኖሎጂ የታገዘ ፍትሃዊ፣ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት መሰጠቱ የዜጎችን የመረጃ ባለቤትነት አረጋግጧል ሲል አስታውቋል። አዲስ የነዋሪነት መታወቂያ ማውጣትና ማደስ፣የልደት፣የሞት፣ የጋብቻና ጉዲፈቻ ሰርተፍኬት ማግኘት በሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ከሚሰጡ አገልግሎቶች መካከል ተጠቃሽ ናቸው። ዲጂታል የሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎትን በሚመለከት ኢዜአ በጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ ዘጠኝ እና በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 16 በመገኘት አገልግሎት አሰጣጡን ቃኝቷል። በጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ ዘጠኝ የጋብቻ ስነ-ስርዓታቸውን ሲፈጽሙ ያገኘናቸው አቶ እያሱ ዋልተንጉስ እና ወይዘሮ ሰላማዊት አክሊሉ የጋብቻ ምስክር ወረቀት ለማግኘት የተሰጣቸው አገልግሎት ቀልጣፋና ዘመናዊ መሆኑን ተናግረዋል። አቶ እያሱ ለኢዜአ በሰጠው አስተያየት፥ በወረዳው ያለው የሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ዲጂታላይዝ መደረጉ ቀልጣፋ አገልግሎት ለማግኘት እንዳስቻላቸው ገልጿል። አቶ ሔኖክ ከፍያለውና ወጣት ከተማ አዲስአለም በሰጡት አስተያየት ቀደም ሲል የሲቪል ምዝገባና ወሳኝ ኩነት አገልግሎቶች የተንዛዙና ለብልሹ አሰራር የተጋለጡ እንደነበር አስታውሰዋል። ይህም ተገልጋዩን ለእንግልትና ለመልካም አስተዳደር ችግር ዳርጎት እንደነበር ገልጸው፥ ተግባራዊ የተደረገው የዲጂታል አሰራር ችግሩን በማቃለል ጥራት ያለው አገልግሎት እንድናገኝ አግዞናል ብለዋል። በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 16 መሰል አገልግሎቶችን ያገኙ ተገልጋዮችም በወረዳው የሚሰጠው የሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት መሻሻሉን ጠቅሰዋል። የልጃቸውን የልደት ካርድ ለማውጣት የመጡት አቶ መለሰ አበራ እንደገለጹት፥ በወረዳው በተለያዩ ወቅቶች በርካታ አገልግሎቶችን ማግኘታቸውን ጠቁመዋል። ጽህፈት ቤቱ ቀደም ሲል የነበረበት ቦታ ለአቅመ ደካሞችና ለአካል ጉዳተኞች ምቹ ካለመሆኑ ባሻገር የነበረው አሰራር እምብዛም መሆኑን ያስታውሳሉ። ወይዘሮ የሺወርቅ ግርማ በበኩላቸው፥ ቀደም ሲል ቀናትንና ወራትን የሚፈጁ አገልግሎቶች በአንድ ቀን መጠናቀቅ መጀመራቸው በአሰራሩ ላይ ትልቅ መሻሻል እንደተደረገበት ያሳያል ብለዋል። ተገልጋዮቹ እንደገለጹት ወረዳው በአሁኑ ወቅት ከተቋም ግንባታ ጀምሮ አሰራሩን ዲጂታላይዝ ማድረጉ ፍትሃዊና ተአማኒ አገልግሎት ለመስጠት አስችሎታል ነው ያሉት። የአዲስ አበባ የሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮናስ አለማየሁ እንደገለጹት፥ ተቋሙ አገልግሎት አሰጣጡን ለማዘመን ያካሔደው ሪፎርም ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል። ሪፎርሙ በዋናነት በዘርፉ የነበረውን ብልሹ አሰራር መቅረፍ፣ በቴክኖሎጂ የተደገፈ ፈጣን አሰራርን ማስረጽና ምቹ ከባቢያዊ የስራ ሁኔታን መፍጠር ላይ ትኩረት ያደረገ ነው ብለዋል። ኤጀንሲው በከተማዋ በ12 ቱም ክፍለ ከተሞች በሚገኙ 119 ወረዳዎች አገልግሎቶቹን በዲጂታል ቴክኖሎጂ አስደግፎ ተግባራዊ ማድረጉን አስታውቀዋል። አሰራሩ ቀደም ሲል በተቋሙ ይታይ የነበረውን ህገ-ወጥ አሰራር፣ የሃሰተኛ ሰነድ ዝግጅትና ስርጭትን ለመከላከል፣ለመቆጣጠርና ተጠያቂነትን ለማስፈን ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ነው ያሉት። በተቋሙ የአገልግሎት ክፍያን ጨምሮ ሁሉም አገልግሎቶች ዲጂታላይዝ በመደረጋቸው የተቋሙን አገልግሎት አሰጣጥ ከማዘመን ባሻገር ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሒደት ውስጥ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛልም ብለዋል። ዲጂታል የሲቪል ምዝገባና የነዋሪነት አገልግሎት የአሠራር ሥርዓት በተቋሙና በነዋሪዎች መካከል ግልጽ አሰራር እንዲዘረጋ በማስቻል የመረጃ ባለቤትነት እንዲረጋገጥ ማስቻሉን ዋና ዳይሬክተሩ አክለዋል።
ለውጪ ገበያ ለሚቀርቡ የግብርና ምርቶች መልከዓ ምድራዊ አመላካች ጥበቃ ማድረግ የሚያስችል ዝግጅት እየተከናወነ ነው - የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን
Jun 3, 2025 129
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦ ለውጪ ገበያ ለሚቀርቡ የግብርና ምርቶች መልከዓ ምድራዊ አመላካች ጥበቃ ማድረግ የሚያስችል ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን አስታወቀ። የመልክዓ ምድራዊ አመላካች የግብርና እና ዕደ-ጥበብ ምርቶች ጥበቃ ላይ ያተኮረ ዓለም አቀፍ ጉባዔ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።   የምርቶች መልከዓ ምድራዊ አመላካች ጥበቃ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለምትታወቅባቸው የግብርና ምርቶች ጣዕምና ልዩ ባህሪ ዕውቅና በመስጠት የተሻለ ዋጋ እንዲያገኙ ያስችላል ተብሏል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር) በጉባዔው መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ ለአዳዲስ ፈጠራዎችና ቴክኖሎጂዎች የተለየ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች ነው። በዚህም ለአምራቾች የተለየ የምርት ዕውቅና መስጠት ፈጠራን ማበረታታት እንደሆነም አንስተዋል። የአለም አእምሯዊ ንብረት ድርጅት(WIPO) ዳይሬክተር ጀነራል ዳረን ታንግ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በርካታ የግብርና ምርቶችን ለዓለም ገበያ በማቅረብ ብትታወቅም የምርቶቹን መገኛ ቦታና ልዩ ባህሪ የሚያመላክት መልከዓ ምድራዊ ጥበቃ ላይ የህግ ማዕቀፍ ሳታዘጋጅ መቆየቷን ተናግረዋል። በዚህም የኢትዮጵያ የግብርና ምርቶች ልዩ ጣዕምና ባህሪ በትክክል እንዳይታወቅና አምራቾቹም ተገቢውን የኢኮኖሚ ጥቅም እንዳያገኙ ማድረጉን አመልክተዋል። እንደ ሀገር ለግብርና ምርቶች መልከዓ ምድራዊ ጥበቃ ማድረግ የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት መጀመሩ ወሳኝና ትክክለኛ እርምጃ መሆኑን ነው ያነሱት።   የኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል በበኩላቸው በመገኛ ምንጫቸው ተለይተው የሚታወቁ የግብርና ምርቶች ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ በመሆን የተሻለ ዋጋ ያወጣሉ ብለዋል። አሁን ላይ በግብርና ምርቶች መገኛና ልዩ ባህሪ ላይ የዳሰሳ ጥናት በማድረግ ዕውቅና የሚያገኙበትን ሥርዓት መዘርጋት የሚያስችል ረቂቅ የህግ ማዕቀፍ ተዘጋጅቷል ብለዋል። ረቂቅ የህግ ማዕቀፉ የተለያዩ ሀገራት የተሻለ ተሞክሮ ተቀምሮበት ለሚመለከታቸው አካላት እንደሚቀርብ ጠቁመው፤ ከአንድ ዓመት በኋላ ወደ ስራ ይገባል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። እንደ ዋና ዳይሬክተሩ ገለጻ፣ ቡናን ጨምሮ ወደ ውጪ የሚላኩ የግብርና ምርቶች ከምንጫቸው በአግባቡ ተለይተውና ዕውቅና ተሰጥቷቸው ወደ ገበያ ባለመቅረባቸው አምራቹ ተገቢውን ጥቅም እንዳያገኝ አድርጓል። የህግ ማዕቀፉ ተግባራዊ ሲሆን፤ የእያንዳንዱ ምርትን ልዩ ባህሪ የያዘ መጽሃፍ እንዲታተም በማድረግ ገዥው ስለምርቱ በቂ ግንዛቤ ይዞ እንዲገዛና ተመሳስሎና ከሌላ ምርት ጋር ተደባልቆ ከሚመረት ተመሳሳይ ምርት እንዲለይ ያደርጋል ብለዋል።
የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ምሁራን አምራች ዜጋ በማፍራት በኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ ነው
Jun 3, 2025 85
አዲስ አበባ፤ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ምሁራን ክህሎት ያለው አምራች ዜጋ በማፍራት በኢኮኖሚ ልማት ላይ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስዳደር ’’የበቃ አሰልጣኝ፤ ክህሎት የጨበጠ ወጣት፤ ለበለጸገ ሀገር’’ በሚል መሪ ሃሳብ ከቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ዲኖችና አሰልጣኝ መምህራን ጋር የምክክር መድረክ አካሂዷል።   የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃንጥራር ዓባይ በመድረኩ ላይ ባለፉት ሁለት ሳምንታት የተለያዩ የሙያ ዘርፎችን ከወከሉ አካላት ጋር ገንቢ ምክክር መደረጉን አስታውሰዋል። ከቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ምሁራን ጋር የተደረገው መድረክም የመዲናዋን ኢኮኖሚያዊ፣ማህበራዊና ፖለቲካዊ ስኬቶች ማስቀጠል በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ለመምከር ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የዕድገት ታሪክ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ምሁራን ለመካከለኛው ኢንዱስትሪ ክህሎት ያላቸው ሙያተኞችን በማፍራት በኢኮኖሚ ልማት ላይ ጉልህ ሚና እየተጫወቱ መሆኑን አስታውቀዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያን የዕድገት ፍላጎትን ታሳቢ በማድረግ ብቃትና ክህሎት ያላቸው ዜጎችን በማፍራት የመዲናዋን ሁለንተናዊ ስኬት ማስቀጠል እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል። ከቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ዲኖችና አሰልጣኝ መምህራን የሚነሱ ሃሳቦች ለመዲናዋ ዘላቂ ዕድገት አዎንታዊ ሚናን በመወጣት ለፖሊሲ ግብዓትነት ጭምር እንደሚውሉ አስረድተዋል። የውይይቱ ተሳታፊ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና አሰልጣኝ መምህራን በመዲናዋ በአጭር ጊዜ በጥራት የተገነቡ ግዙፍና ሰው ተኮር የልማት ስራዎች የሚደነቁ መሆናቸውን ገልጸዋል። የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ያፈሯቸው ክህሎት ያላቸው ሙያተኞችም በኮሪደርና በኢንተርፕራዝ ልማት ላይ አዎንታዊ ሚና እየተጫቱ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የተቋማቱ መምህራን የሚያነሷቸው የመኖሪያ ቤት፣ የትራንስፖርት፣ የገበያና የተቋማዊ የአሰራር ማሻሻያዎችም ምላሽ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል። ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ በምላሻቸው÷ በመዲናዋ የነዋሪዎችን ጫና የሚያቃልሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችና ሰው ተኮር የልማት ስራዎች መሰራታቸውን አንስተዋል። በመኖሪያ ቤት ልማት ዘርፍም በተለያዩ አመራጮች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን ገልጸዋል። በየትኛውም ኢንቨስትመንትና ኢንተርፕራይዝ ልማት የቴክኒክና ሙያ አሰልጣኞች ክህሎትና ብቃት ያላቸው አምራች ሙያተኞችን ማፍራት እንደሚኖርባቸው አስገንዝበዋል።   በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ጥራቱ በየነ÷ ኢትዮጵያ ፀጋዋን በመጠቀም በሁሉም መስክ ብልጽግናን እንደምታረጋግጥ ጠቅሰው፤ በአጭር ጊዜ የተመዘገቡ የልማት ስኬቶችም ማሳያ ናቸው ብለዋል። የቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ተቋማት ክህሎት የተላበሰ አምራች ዜጋ ማፍራት አለባቸው ብለዋል።
በእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ላይ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን በመፍታት የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብርን ውጤታማነት ለማስቀጠል ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 3, 2025 81
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦ በእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ላይ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን በመፍታት የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብርን ውጤታማነት ለማስቀጠል እየተሰራ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። በሚኒስቴሩ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አስራት ጤራ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በእንስሳት ዝርያ በተለይ የዳልጋ ከብቶችን ዝርያ በማሻሻል የወተት ምርታማነትን ለማሳደግ ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሶዶ ዳልጋ ከብቶች ዝርያ ማሻሻያ ማዕከል የተገነባው የፈሳሽ ናይትሮጂን ማምረቻም ከኮርማ የሚገኘውን ዘር ሳይበላሽ በህይወት ለማቆየትና ከአንዱ ኮርማ የተገኘውን የዘር ፍሬ ለበርካታ ላሞች ለማዳቀል እንደሚያስችል ጠቁመዋል። ይህም አርሶ አደሩና በእንስሳት ልማት ላይ የተሰማሩ ከሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር የተሻለ ተጠቃሚ እንዲሆኑና የምግብ ዋስትናቸውን እንዲያረጋግጡ ያግዛል ብለዋል። ቀደም ሲል የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የፈሳሽ ናይትሮጂን እጥረት ከፍተኛ ችግር እንደነበር ያስታወሱት ደግሞ የሶዶ ዳልጋ ከብቶች ዝርያ ማሻሻያ ማዕከል ኃላፊ ምህረቱ ማርቆስ ናቸው። በአሁኑ ወቅት ማዕከሉ ተገንብቶ ሥራ መጀመሩ የፈሳሽ ናይትሮጂን ምርትን በማሳደግ ችግሩን ሙሉ በሙሉ መፈታቱን ገልጸዋል። የፈሳሽ ናይትሮጂን ማምረቻው የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ሥራውን በማቀላጠፍ የወተት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ አበርክቶው የጎላ ነውም ብለዋል። በወላይታ ሶዶ ከተማ በእንስሳት እርባታ ሥራ የተሰማሩት የኤግዞደስ ፋርም ሥራ አስኪያጅ ተሻለ አላጋው(ዶ/ር) ከዚህ ቀደም የፈሳሽ ናይትሮጂን እጥረት በስራቸው ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ሲያሳድር መቆየቱን አስታውሰዋል። የኮርማውን ዘር ከሩቅ አካባቢዎች ገዝተው በማምጣት ለከፍተኛ ወጪ ሲዳረጉ እንደነበርም ተናግረዋል። የተገዛው ዘርም በፈሳሽ ናይትሮጂን እጥረት ምክንያት በከንቱ ይባክን እንደነበር ጠቅሰው በከተማው ፈሳሽ ናይትሮጂን መመረቱ በአካባቢው በዘርፉ ለተሰማሩ እፎይታ መስጠቱንና ውጤታማ እንደሚያደርግም ገልጸዋል። መንግስት የግብዓት እጥረቶችን በመፍታት የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብርን ለማጠናከር እያሳየ ያለው ቁርጠኝነት መጠናከር ለምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ ያበረክታል ነው ያሉት። በወላይታ ሶዶ ከተማ ከ63 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባው የፈሳሽ ናይትሮጂን ማምረቻ፣ ማቀነባበሪያና ማሰራጫ ማዕከል የፌደራልና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች በተገኙበት በቅርቡ ተመርቆ ሥራ መጀመሩ የሚታወስ ነው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም