ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል እና አገልግሎቶቹን የማስፋት ሥራ እየተከናወነ ነው
Dec 14, 2025 53
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 5/2018(ኢዜአ)፡- መሶብ የአንድ ማዕከልንና የሚሰጡ የአገልግሎት ዓይነቶችን ለማስፋት እየተሠራ መሆኑን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሠመረ ጂራታ(ኢ/ር) ተናገሩ። ለዜጎች የሚሰጥ አገልግሎት ከቅሬታ የጸዳ፣ ጊዜና ወጭ ቆጣቢ፣ ፍትሐዊ ብሎም ተደራሽ እንዲሆን ማስቻል የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ዓላማ መሆኑን አስገንዝበዋል። እንደ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከመስከረም 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአምሥት የክልል እና በሦስት የፌደራል ተቋማት በ33 ዘርፎች አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። እስካሁንም ከ6ሺህ 300 በላይ ተገልጋዮች አገልግሎት ማግኘታቸውን አስታውቀዋል። በቀጣይ ወደ ማዕከሉ የሚገቡ ተቋማትና አገልግሎቶችን ቁጥር የማስፋት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። በዚህም መሠረት ተጨማሪ አንድ የፌደራል እና ሦስት የክልል ተቋማት ወደ መሶብ የአንድ ማዕከል መግባት የሚያስችላቸውን ሥራ እያከናወኑ ነው ብለዋል። ይህን ተከትሎም በአጭር ጊዜ አምሥት ተጨማሪ አገልግሎቶች ወደ ማዕከሉ እንደሚገቡ አመላክተዋል። በሌላ በኩል በአሶሳ ከተማ አሥተዳደር ደረጃ መሶብ የአንድ ማዕከል እንዲኖር እየተሠራ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
በክልሉ የኮደርስ ስልጠና መርሐ ግብር በተጠናከረ መልኩ እየተከናወነ ነው
Dec 13, 2025 126
ሚዛን አማን ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ):- የኮደርስ ስልጠና መርሃ ግብር በተጠናከረና በተቀናጀ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ አስታወቀ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለ5 ሚሊዮን ዜጎች ነፃ የኮደርስ የስልጠና እድል በመመቻቸቱ እስካሁን በርካቶች የእድሉ ተጠቃሚ ሆነዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ምትኩ አስፋው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ 138 ሺህ ዜጎችን ለማሰልጠን ዕቅድ የተያዘ ሲሆን ከእነዚህም መካከል እስካሁን 16 ሺህ 700 የሚሆኑት ስልጠናውን አጠናቀው የምሥክር ወረቀት አግኝተዋል። በተያዘው ዓመትም የስልጠናው ሂደት ተጠናክሮ የቀጠለ በመሆኑ ተጨማሪ 63 ሺህ ዜጎችን የማሰልጠን እቅድ ተይዞ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የስልጠናው ዓላማ በዘርፉ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሆኑ ዜጎችን ማፍራት መሆኑን የተናገሩት ኃላፊው የእድሉ ተጠቃሚ ለመሆን ጊዜ ሳያባክኑ መመዝገብና መሰልጠን ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። ሥልጠናውን ወስደው ሰርተፊኬት ከተቀበሉት መካከል የሲዝ ከተማ አስተዳደር ነዋሪው ወጣት ምናሉ ግዛቸው፤ በሥልጠናው ከዘመኑ ጋር ተወዳዳሪ እንድሆን የሚያስችለኝን እውቀት አግኝቻለሁ ብሏል።   በወሰዳቸው አራት ኮርሶች ከመሠረታዊ የኮምፒዩተር እውቀት ጀምሮ አርተፊሻል ኢንተለጀንስ እና ፕሮግራሚንግ ላይ በቂ ክህሎት ማግኘቱን ተናግሯል። የሥልጠና አሰጣጥ ሁኔታው ቀላልና ለመያዝ ምቹ በመሆኑ ማንኛውም ሰው ጊዜ ብቻ ሰጥቶ ዕድሉን መጠቀም እንዳለበት ነው የተናገረው።
ሰልጣኞች በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ቴክኖሎጂ ዕውቀታቸው ዳብሯል
Dec 13, 2025 152
አርባምንጭ ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ):- የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የቴክኖሎጂ ዕውቀታቸውን እንዳዳበረው የአርባምንጭ ከተማ ሠልጣኞች ገለጹ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የአርባ ምንጭ ከተማ የኢትዮ-ኮደርስ ሰልጣኞች መካከል ወጣት ሊዲያ ዳሾ፤በአንድሮይድ ደቨሎፕመንት፣ ዳታ አናሊስስ፣ አርተፊሻል ኢንተለጀንስና ፕሮግራሚንግ ዘርፎች ስልጠና በመከታተል በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርጋትን የምስክር ወረቀት መውሰዷን ገልጻለች። ወቅቱ የሚጠይቀውን የሰው ሠራሽ አስተውሎት ዕውቀት መያዝ አስገዳጅ በመሆኑ ለዚሁ ራሷን ማብቃቷን አስረድታለች።   የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የኦን ላይን ሥራዎችን ለመወዳደርና የሥራ ዕድሎችን ለመፍጠር ምቹ ሁኔታ ያለው መሆኑንም ተናግራለች፡፡ ሌላኛው ሠልጣኝ ወጣት ኦሳ ፋንታ በበኩሉ፤ በፕሮግራሚንግ እና ኮዲንግ ዘርፎች ስልጠና በመውሰድ የምስክር ወረቀት አግኝቷል። ስልጠናው ወቅቱን የዋጀ የቴክኖሎጂ ክህሎት በማላበስ አለም አቀፍ ተወዳዳሪነቱን እንደሚጨምርለት ተናግሯል።   የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መንግስት ወጪውን መሸፈኑ ዜጎችን ለማብቃትና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለማድረግ የታለመ ትልቅ ዕድል ነው ብሏል። የምስክር ወረቀቱ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ያለው መሆኑ በየትኛውም ሀገር የሥራ እድልን ለማግኘት መሰረት እንደሚጥል ገልጿል። የአርባምንጭ ከተማ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ሃላፊ አቶ በሃይሉ ካፒቴን ፤ መንግስት የዜጎችን የቴክኖሎጂ ዕውቀት ለማሳደግ የጀመረው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በርካታ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረጉን ተናግረዋል።   በተለይ ለወጣቶች ዕውቀታቸውን በማሳደግ ለስራ ፈጠራ በማዋል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንዲያሳድጉ የሚረዳ ነው ብለዋል፡፡ የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና እንደ ሀገር ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በአርባምንጭ ከተማ 4 ሺህ 455 ዜጎች ስልጠና ወስደው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም 4 ሺህ ዜጎችን ለማሠልጠን ግብ ተይዞ እየተሰራ ሲሆን በእስካሁኑ 2 ሺህ 829 ዜጎች መሠልጠናቸውን ገልጸዋል።
አዲሱ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግር አቅም ይሆናል
Dec 13, 2025 119
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ አዲሱ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግር አቅም እንደሚሆን የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴዔታ ተሻለ በሬቻ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠንካራ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ተቋማትን በመገንባት በእውቀትና ክህሎት የበቃ የሰው ኃይል ማፍራት የሚያስችል አዲስ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ ተዘጋጅቶ ስራ ላይ መዋሉ ይታወቃል። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴዔታ ተሻለ በሬቻ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ አዲሱ ስትራቴጂ የአረንጓዴ የክህሎት ልማት የስልጠና ፕሮግራሞችን የያዘ እና ለታዳሽ ኃይል ትኩረት የሰጠ ነው። ወደ አረንጓዴ ኢኮኖሚ በሚደረገው ሽግግር ብቃትና ክህሎት ያለው የሰው ኃይል ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ስትራቴጂው ብቃት ያለው እና ለአካባቢ ተስማሚ ቴክኖሎጂዎችን የሚተገብርና ሃብትን በቁጠባ የሚጠቀም ትውልድ ለመገንባት እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡ ሥርዓተ-ትምህርቶችን በአረንጓዴ የስራ መርሆዎችና አሠራሮች በማበልጸግ ተማሪዎች ከተቋማት ሲወጡ ለአካባቢ ተስማሚ የሆኑ ዘዴዎችንና መሣሪያዎችን እንዲጠቀሙ ያስችላል ብለዋል፡፡ አዲሱ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግር አቅም እንደሚሆንም ነው ሚኒስትር ዴዔታው የተናገሩት፡፡ በአዲሱ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ መሰረት የአረንጓዴ ቴክኒክና ሙያ ልጠና ፓኬጅ ተቀርጾ ወደ ስራ መግባቱን አመላክተዋል፡፡፡ ይህ ፓኬጅ ከብክለትና ከብክነት የጸዳ የሃይል አጠቃቀም እንዲኖር ያስችላል ብለዋል፡፡ በተቋማት ውስጥ ዘመናዊ እና ለአካባቢ ተስማሚ የሆኑ የማሰልጠኛ መሣሪያዎችን በማስገባት ተማሪዎች በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እንደሚሰራም ተናግረዋል፡፡ ተማሪዎች በንድፈ ሃሳብ ብቻ ሳይሆን በዘመናዊ አረንጓዴ ቴክኖሎጂዎች ተግባራዊ ልምምድ በማድረግ በሥራ ዓለም ውስጥ የአረንጓዴ ልምዶችን የመተግበር ብቃት እንዲኖራቸው እየተደረገ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ከዓለም አቀፍ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ መስፋፋት ጋር ተያይዞ የሚፈጠሩ አዳዲስ የስራ ዕድሎችን መጠቀም እንደሚያስችልም እንዲሁ፡፡
በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሰጣጥ ቀልጣፋ አገልግሎት እያገኘን ነው - ተገልጋዮች
Dec 13, 2025 104
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 4/2018(ኢዜአ)፡- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እያገኘነው ያለው አገልግሎት ፈጣን እና እንግልትን የቀረፈ ነው ሲሉ ተገልጋዮች ገለጹ። በማዕከሉ አገልግሎት አግኝተው ሲመለሱ ኢዜአ ያነጋገራቸው ተገልጋዮች እንዳሉት፤ ነባሩ አገልግሎት አሰጣጥ ከአንዱ ወደ ሌላው ተቋም መመላለሱ ብሎም ቶሎ ጉዳይን ለመፈጸም አድካሚና የቅሬታ ምንጭ ነበር። አቶ ሙፍቲ መርቀኒ ለዓመታት አገልግሎት ለማግኘት ወደ ተቋማት ይመላለሱ እንደነበር አውስተው፤ ያኔ አገልግሎት አሰጣጡ ረጅም ጊዜ የሚወስድና ጉዳያቸውም ውሎ ያድር እንደነበር አስታውሰዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሥራ ከጀመረ ወዲህ አራት ጊዜ ለአገልገሎት መምጣታቸውንና በርካታ ተቋማት በአንድ ቦታ በመኖራቸው ጉዳያቸውን በቀላሉ መፈጸም መቻላቸውን ተናግረዋል።   የንግድ ፈቃድ ለማውጣት ወደ ማዕከሉ መምጣታቸውን ጠቁመው፤ ከጠበቁት በተሻለ ፍጥነት በመስተናገዳቸው በአገልግሎቱ መርካታቸውን አስታውቀዋል። አክሲዮን ለማሻሻል፣ የንግድ ምዝገባ ለማከናወንና የንግድ መለያ ቁጥር ለማውጣት ወደ ማዕከሉ ያቀኑት ዝነኛው መዝገቡ በበኩላቸው፤ በ20 ደቂቃ ውስጥ ቀልጣፋ አገልግሎት በማግኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። ዛሬን ጨምሮ በማዕከሉ ሁለት ጊዜ አገልግሎት ለማግኘት በማዕከሉ መገኘታቸውን ጠቁመው፤ አገልግሎት አሰጣጡ ምቹ እና ድካምን ያስቀረ ነው ብለዋል። ጽጌ ዳኛው በበኩላቸው ማኅበር ለማጸደቅና ስያሜ ለማውጣት ወደ ማዕከሉ መምጣታቸውን ጠቅሰው፤ በአምሥት ደቂቃ ውስጥ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ማዕከሉ ከመጀመሩ በፊት ግን የሲስተም ችግር፣ የተቋማት በተለያየ ቦታ መሆንና የወረፋ መብዛትን ተከትሎ መስተጓጎል ያጋጥም እንደነበር አውስተዋል። ለተለያዩ አገልግሎቶች በተደጋጋሚ ወደ ማዕከሉ መምጣታቸውን አንስተው፤ ከበር ጀምሮ እስከ መጨረሻ አገልግሎት አሰጣጥ ድረስ ጥሩ አገልግሎት እየተሰጠ እንደሚገኝ መስክረዋል። ከጠበቅነው ጊዜ በተሻለ ፍጥነት ተስተናግደናል ያሉት ተገልጋዮቹ፤ ወጪና ጊዜን በመቆጠብ ብሎም ከአንድ ወደ ሌላ ተቋም በመመላለስ የሚከሰት እንግልትን በማስቀረት በአጭር ጊዜ አገልግሎት አግኝተናል ብለዋል።
ዓለም አቀፍ ሁኔታን ያገናዘበ የጤና ስርዓት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ሰው ሰራሽ አስተውሎት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
Dec 12, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፍ ሁኔታን ያገናዘበ የጤና ስርዓት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ሰው ሰራሽ አስተውሎት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሒ ገለፁ። ጤና ሚኒስቴር "የሰው ሰራሽ አስተውሎትና የቴሌ ጤና ቴክኖሎጂ ለጤናው ዘርፍ የሚኖራቸው የወደፊት ሚና" በሚል መሪ ሀሳብ የባለድርሻ አካላት ውይይት አካሒዷል።   የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሒ እንደገለፁት መንግስት የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል። የጤና አገልግሎትን ከሰው ሰራሽ አስተውሎትና ቴሌ-ጤና ቴክኖሎጂ ጋር በማቀናጀት ተደራሽ እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። ለህክምና አገልግሎት የሚሰበሰቡ መረጃዎች ላይ በመመስረት የሚሰጡ አገልግሎቶችን ለማጠናከር የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን መጠቀም ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። በተለይም በወረርሽኝና በተፈጥሮ አደጋዎች ቅድመ ትንበያና የተቀናጀ ምላሽ አሰጣጥ ላይ አይነተኛ ሚና እንዳለውም ጠቁመዋል። የጤና ስርዓቱን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር አዳዲስና ፈጠራ የታከለባቸው ቴክኖሎጂዎች በተገቢው መልኩ ተግባራዊ እየተደረጉ መሆኑንም አንስተዋል። በ2016 ዓ.ም የተሻሻለው አዲሱ የጤና ፖሊሲ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ በተገቢው መልኩ ጥቅም ላይ መዋሉን የሚደግፍ መሆኑ ለአተገባበሩ አስቻይ ሁኔታ መፍጠሩን ነው የጠቀሱት። በተለይም ለጤና ምርመራ፣ በታካሚዎች መረጃና የህክምና ታሪክ ላይ የተመሠረተ አገልግሎት ለመስጠትና በርቀት ለሚሰሩ የቴሌ ጤና አገልግሎት መጠናከር ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። ዓለም አቀፍ ሁኔታን ያገናዘበ የጤና ስርዓት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን ሀላፊነት እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።   በጤና ሚኒስቴር የጤና ስርዓት ኢኖቬሽንና ጥራት መሪ ስራ አስፈጻሚ ዶክተር አባስ ሃሰን በበኩላቸው፤ የጤና አገልግሎት ጥራትን በማረጋገጥ ሒደት ባለድርሻ አካላት ያላቸው ሚና የጎላ መሆኑን ገልጸዋል። የጤናውን ዘርፍ ከሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ ጋር አጣጥሞ ተግባራዊ ለማድረግ ለተጀመረው ጥረት በዘርፉ የሚሰሩ ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን ድጋፍ እያደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል። በኢትዮ-ቴሌኮም የኢንተርፕራይዝ ሶሉዩሽን ቺፍ ኦማድረግ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   በዚህም የጤና ስርዓቱን የሚያዘምኑ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች በጤና ተቋማት ተግባራዊ መደረግ መጀመራቸውን ነው የጠቀሱት። የጤና ተቋማትን በአንድ ቋት በማስተሳሰር መረጃን በቀላሉ ማግኘት የሚያስችለው ቴክኖሎጂ በጋራ ትብብር መልማቱን አንስተዋል።
አገልግሎቱ አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረጉ ቀልጣፋና አስተማማኝ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል
Dec 12, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረጉ ቀልጣፋና አስተማማኝ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ተገልጋዮች ገለጹ። የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቶፊክ ሻፊ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት አገልግሎቱ አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረጉ ደንበኞች ቀልጣፋና አስተማማኝ መስተንግዶ እያገኙ ነው። አገልግሎቱ ሀሰተኛ ሰነዶችን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር የቴክኖሎጂ ትስስር መፍጠር በመቻሉና የፋይዳ መታወቂያን በአስገዳጅነት በመጠቀሙ ችግሩን በመከላከል ረገድ ውጤታማ ስራ ማከናወኑን ገልጸዋል። የመረጃ ቋት ስርዓት በመዘርጋት ሀገራዊ ሰነድ የማረጋገጥና የመመዝገብ ስራ እየተከናወነ መሆኑንም አስታውቀዋል። የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓትን በማጠናከርና ተደራሽነትን በማስፋት ተገልጋዮች ያለ ወረፋ እንዲስተናገዱ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም ተናግረዋል። በዚህም አገልግሎቱ ባሉት ቅርንጫፎች ለተገልጋዮች ፍላጎት ፈጣን ምላሽ በመስጠት ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። ተቋሙ በአጠቃላይ ከወረቀት ወደ ዲጂታላይዜሽን የሚያደርገው ሽግግር በተሳካ ሁኔታ እየሄደ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። የንግድና ኢንቨስትመንት ስራዎች እንዲሳለጡና የማህበራዊ መስተጋብር ጤናማነት እንዲረጋገጥ አገልግሎቱ የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ ተገልጋዮች በበኩላቸው በተቋሙ ባገኙት አገልገሎት ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል አቶ ከበደ ወልደጊዮርጊስ እንዳሉት ተቋሙ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ እየሰጠ ባለው ቀልጣፋ አገልግሎት በመታገዝ በአጭር ጊዜ ጉዳያቸውን አጠናቀው መመለስ ችለዋል። በተቋሙ እየተሰጠ ያለው አገልግሎት ከዚህ በፊት ከነበረው አንጻር መሻሻሉንም ነው የተናገሩት። ወይዘሮ ዘሃራ መሀመድ በበኩላቸው ባገኙት አገልግሎት መደሰታቸውን ገልጸው የሚሰጠው አገልግሎት ከነበረው በእጅጉ መሻሻሉን ገልጸዋል። በዚህም በምቹ የአገልግሎት መስጫ ቦታ በአጠረ ጊዜ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘታቸውን ነው የጠቆሙት። የተቋሙ የአገልግሎት አሰጣጥ በቴክኖሎጂ የታገዘ እና ቀልጣፋ በመሆኑ ጥሩ አገልግሎት ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ አቶ አንዋር አህመድ ናቸው። ቀደም ሲል ከወረፋ ጋር በተያያዘ ይታዩ የነበሩ ችግሮች አሁን ላይ መቀረፋቸውን ተናግረዋል።
የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎትን በማዘመን ህብረተሰቡ ፈጣንና ወጪ ቆጣቢ አገልግሎት እንዲያገኝ እየተደረገ ነው
Dec 12, 2025 92
አሶሳ፤ ታህሳስ 3/2018 (ኢዜአ)፦ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎትን በማዘመን ህብረተሰቡ ፈጣንና ወጪ ቆጣቢ አገልግሎት እንዲያገኝ እየተደረገ መሆኑን የፌዴራል የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሀሚድ ኪኒሶ ተናገሩ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፍትህ ቢሮ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባን በዲጂታል የታገዘ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል።   በዕለቱ የተገኙት የፌደራል የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሀሚድ ኪኒሶ እንደተናገሩት፤ ዜጎች በሁሉም ዘርፍ በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት እንዲያገኙ በማድረግ ብልሹ አሰራርን ለማስቀረት እየተሰራ ነው። የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት በርካታ ተገልጋዮችን የሚያስተናግድ በመሆኑ በሀገር አቀፍ ደረጃ አገልግሎት አሰጣጡን የማዘመን ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ሀረሪ፣ ሲዳማና አማራ ክልሎች ዲጂታል የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት እያከናወኑ መሆኑን የተናገሩት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፍትህ ቢሮም በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ስራ መግባቱን ጠቁመዋል። አገልግሎቱ ዲጂታል መሆኑ ተዓማኒነት ያለው አሰራርን ከመፍጠር ባለፈ የመረጃ ደህንነትን በመጠበቅ አበርክቶው የጎላ ነው ብለዋል።   የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ እና የክልሉ ፍትህ ትራንስፎርሜሽን ሰብሳቢ ወይዘሮ አስካለች አልቦሮ በበኩላቸው፤ አገልግሎቱ የዜጎችን እንግልት የሚያስቀር እና በተገልጋዩና በመንግስት ተቋማት መካከል ያለውን መተማመን ለማሳደግ ያግዛል ብለዋል። በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ጨምሮ ተቋማት በራሳቸው አቅም አሰራራቸውን በማዘመን የዲጂታል አገልግሎት እንዲስፋፋ እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰዋል። በክልሉ የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎትም በቴክኖሎጂ የታገዘ በመሆኑ በቢሮው የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን የሚቀርፍ ነው ያሉት ደግሞ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፍትህ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሙሐመድ ሀሚድ ናቸው።   በቀጣይም የዲጂታል አሰራሩን እስከታችኛው መዋቅር በማውረድ ዘርፉን የማዘመን እና አገልግሎት አሰጣጡን የተሳለጠ ለማድረግ እንደሚሰራም አስታውቀዋል።
የኮደርስ ስልጠና የመንግስት አገልግሎትን ለማዘመን አግዟል
Dec 12, 2025 104
አዶላ ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ የኮደርስ ስልጠና የመንግስት አገልግሎትን ለማዘመን እንዳገዛቸው የጉጂ ዞን የመንግስት ሰራተኞች ገለጹ፡፡ በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከወሰዱ የአዶላ ከተማ የመንግስት ሰራተኞች መካከል ወጣት ጉደታ ገመዳ አንዱ ነው፡፡ ስልጠናው ራስን በቴክኖሎጂ በማብቃት ለደንበኞች የተቀላጠፈ አገልግሎትን ለመስጠት ተደማሪ አቅም እንደሚሆን ወጣት ገመዳ ተናግሯል።   ከስልጠናው የኮምፒውተር ሳይንስና የሰው ሰራሽ አስተውሎት እውቀትን ማግኘቱ ለስራው ስኬት እንዳገዘው ገልጿል። የወጣት ገመዳን ሀሳብ የሚጋራው ሌላው የከተማው የመንግስት ሰራተኛ ወጣት ደስታ ሀለኬ በበኩሉ ስልጠናው እውቀትና ቴክኖሎጂን በማቀናጀት ተወዳዳሪነቱን እንዳሳደገው ተናግሯል። ስልጠናውን በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት መውሰዱን ገልፆ ስልጠናው የዜጎችን ብቃትና ተወዳዳሪነት በማሳደግ ለተሻለ ስራ የሚያነሳሳ ነው ብሏል፡፡   ይህን እድል በመጠቀም የዘመነ አሰራር ለመተግበር በእውቀትና ክህሎት ለማበልጸግ ሁሉም ሰው ስልጠናውን በመውሰድ ለሀገር ልማት የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባም ልምዱን አካፍሏል፡፡ የዞኑ ሲቪል ሰርቪስ ጽህፈት ቤት የሰው ሀብት ልማትና ስምሪት ቡድን መሪ አቶ ቢሉ ሶርሳ፤ የመንግስት ሰራተኞችን እውቀትና ክህሎት ለማሳደግ 25 ሺህ ሰራተኞች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እንዲወስዱ መታቀዱን ገልጸዋል።   ስልጠናው የዲጂታል ኢኮኖሚን ለመገንባት የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ መሆኑን ጠቁመው በእስካሁኑም 23 ሺህ 456 ሰራተኞች ስልጠናውን አጠናቀው የምስክር ወረቀት መውሰዳቸውን ጠቁመዋል፡፡ ስልጠናው የመንግስት ሰራተኞችን ከቴክኖሎጂው ዓለም ጋር በማስተዋወቅ ብቁና ተወዳዳሪ የሚያደርግ አሰራርን እንዲከተሉ ማለሙን አክለዋል፡፡ ይህም በቴክኖሎጂ የተደገፈ ፈጣንና መንግስታዊ አገልግሎት ለመስጠት የሚያግዝ መሆኑንም አመልክተዋል፡፡
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ብልሹ አሠራሮችን አስቀርቷል
Dec 12, 2025 72
አዲስ አበባ፤ታኅሣስ 3/2018 (ኢዜአ)፡-መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ብልሹ አሠራሮችን በመቅረፍ እርካታ በተሞላበት አግባብ አገልግሎቶች እንዲቀርቡ ማስቻሉ ተገለጸ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አሥራት አዳሮ እንዳሉት፤ ማዕከሉ የተንዛዛና ለብልሹ አሠራር የተጋለጠውን የተቋማት አገልግሎት ከብልሹ አሠራር በፀዳ መልኩ ለማቅረብ አስችሏል። ተደራሽ አገልግሎት በመስጠት የዜጎችን እርካታ ማረጋገጥ እና ይባክን የነበረውን የሰው ኃይል፣ ጊዜ፣ ጉልበት ብሎም ሀብት ከብክነት ማዳኑንም ገልጸዋል። በክልሉ ከጥቅምት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአንድ ማዕከል አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑንም አውስተዋል። አገልግሎቱ የተጀመረው በዘጠኝ ተቋማት በ28 አገልግሎት መሆኑን ገልጸው፤ አሁን ላይ አገልግሎቱ ወደ 35 ማደጉን አረጋግጠዋል። ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ጊዜም 3 ሺህ 641 ሰዎች አገልግሎቱን በአንድ ማዕከል ማግኘታቸውን ለኢዜአ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት በአምስት የዞንና የከተማ አሥተዳደሮች መሶብ የአንድ ማዕከልን ለማስፋፋት ጥረት እየተደረገ መሆኑን አመላክተዋል።
የሳይበር ጥቃት ተጋላጭነትን ለመቀነስ...
Dec 12, 2025 147
በአብዛኛው ለጥቃት ተጋላጭ የሆኑት የፋይናንስ ተቋማት እና ባንኮች መሆናቸውን የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር አስገነዘበ። በአስተዳደሩ የሳይበር መከላከል ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር መሀመድ ፈረጃ፤ የፋይናንስ ተቋማት፣ሚኒስቴሮች፣ የሕክምና ተቋማት፣ ዩኒቨርሲቲዎች፣ የቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢ ተቋማት፣ የጸጥታና ደኅንነት ተቋማት እንዲሁም ሚዲያዎች በተደጋጋሚ የጥቃት ዒላማ እንደሚደረጉም ተናግረዋል። ስለዚህም የሳይበር ጥቃት ተጋላጭነትን ለመቀነስ ቁልፍ የመሠረተ-ልማት ተቋማትን የሚመሩ አካላት ዘርፉን ወይም ተቋም ተኮር የሳይበር ደኅንነት ፖሊሲዎችን እና ፍሬም ወርኮችን መንደፍ እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል። ከዚህም በተጨማሪ ስታንዳርዶችን እንዲቀርጹ እና አሠራሮች እንዲኖሯቸው ይጠበቃል ነው ያሉት። እነዚህን የአሠራር ሥርዓቶች ወደ መሬት ለማውረድ በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ኃይል እና መሠረተ-ልማቱን ለመጠበቅ የሚያስችል ቴክኖሎጂ እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል። በሰው፣ በአሠራር ሥርዓት እና በቴክኖሎጂ ተቋማት ራሳቸውን ዝግጁ ማድረግ እንዳለባቸውም መክረዋል። የሳይበር ደኅንነትን በተቋማት ለማረጋገጥ ዝቅተኛ የሚባሉትን የደኅንነት መስፈርቶች (Baseline) ማሟላት እና ተግባራዊነታቸውን መከታተል እንደሚጠበቅም አመላክተዋል። ይህንም ለማስቻልም መደበኛ የደኅንነት ዳሰሳና ኦዲት ማከናወን እንደሚጠበቅ ጠቁመዋል። በተጨማሪም ጠንካራ የመከላከል ዐቅም ለመገንባት የ‘ዜሮ ትረስት’ መርኅን ተግባራዊ ማድረግ ይገባል ብለዋል። ይህ ማለትም ቀደም ሲል ስጋት ከውጭ እንጅ ከውስጥ የለም የሚል እንደነበር አውስተው፤ የ‘ዜሮ ትረስት’ መርኅ ግን “ማንንም አለማመን እና ሁሉንም ማረጋገጥ” በሚል የተመሰረት ሲሆን ይህም ስጋት ከውስጥም ከውጭም እንዳለ አምኖ መሥራት ነው ብለዋል። ከላይ ከተገለጹት ጥንቃቄዎች አልፎ የሳይበር ጥቃት ሊያጋጥም እንደሚችል እና የጥቃት ጉዳቱን ለመቀነስ እንዲሁም በጋራ ለመመከት እንዲቻል ከተቋማችን ጋር በቅርበት መሥራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። በአብዛኛው ጊዜ ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭ የሆኑት የፋይናንስ ተቋማት እና ባንኮች መሆናቸውን ዓመታዊ የሳይበር ጥቃት ሪፖርታችን ያመለክታል ብለዋል።
ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ ማዕከል ለመሆን በቁርጠኝነት ትሰራለች 
Dec 11, 2025 98
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ ማዕከል ለመሆንና ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከር በቁርጠኝነት እንደምትሰራ የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፖሻል ኢንስቲትዩት ከውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "ለሰላም፣ ለልማት እና ለጋራ ብልጽግና አህጉራዊ አጋርነትን ማጠናከር" በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጁት አዲስ የህዋ ፎረም ተካሂዷል።   የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አብዲ ዘነበ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢንስቲትዩቱ የኢትዮጵያን ህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማሳደግ እየሰራ ነው። በፍጥነት እያደገ የመጣው የህዋ ሳይንስ በአገራት ልማት አስተዋጽኦው ከፍተኛ መሆኑን አመልክተው፤ በተለይም የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም፣ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ፣ ለሳተላይት ኮሙኒኬሽንና ለሌሎች ስራዎች ማዕከል መሆኑን ገልጸዋል።   በዓለም አቀፍ ደረጃ አፍሪካ በህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ ያላት ውክልና በተቀናጀ መልኩ እንዲከናወን እንሰራለን ብለዋል። ኢትዮጵያ ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከርና በስትራቴጂክ ዲፕሎማሲ ግንባር ቀደም ለመሆን ቁርጠኛ መሆኗንም ገልጸዋል። ፎረሙ አዲስ አበባን በህዋ ሳይንስ ዘርፍ የዲፕሎማሲ ማዕከል ለማድረግ ከሚከናወኑ ተግባራት አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል። በኢንስቲትዩቱ የአፍሪካ ጉዳዮች ከፍተኛ ተመራማሪ ግዛቸው አሥራት (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአፍሪካ የህዋ ሳይንስ ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሰላም ግንባታና የብልጽግና ስራዎችን ለማጎልበት በጋራ እንሰራለን ብለዋል።   ዲፕሎማሲው በዓለም አቀፍ የህዋ ሳይንስ አስተዳደር የአፍሪካን ጥቅም ለማስጠበቅ፣ ትብብርን ለማጠናከር፣ የተፈጥሮ ሀብቶችን ተደራሽነት ለማጠናከር እገዛ እንደሚያደርግም አብራርተዋል። በዘርፉ ምርምርና መረጃ ልውውጥ በማድረግ የአፍሪካን የጋራ አቅምና ቀጣናዊ ትብብር ማሳደግ እንደሚቻል ተናግረዋል። ኢንስቲትዩቱ የእውቀት፣ የቴክኒክና የአቅም ግንባታ ስራዎች ላይ በጋራ ለመስራት ዝግጁ መሆኑንም ገልጸዋል። የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፖሻል ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ይሽሩን አለማየሁ( ዶ/ር)፤ አዲስ አበባ የአፍሪካ መዲና በመሆኗ ለህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ ምቹ ናት ብለዋል።   አዲስ አበባን በዘርፉ የዲፕሎማሲ ማዕከል ማድረግ በዓለም አቀፍ መድረክ የኢትዮጵያንና የአፍሪካን አቅም ለማሳየት የሚያስችል መሆኑን ነው የገለጹት። በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የጂኦ ስፓሻልና ማኔጅመንት ተጠሪ አንድሬ ኖንጉርማ እንደተናገሩት፤ በህዋ ሳይንስ ዘርፍ የአፍሪካውያንን የጋራ ስራ ማጠናከር ያስፈልጋል።   ኢትዮጵያ በዘርፉ ውጤታማ ስራዎች እያከናወኑ ከሚገኙ አገራት አንዷ መሆኗን ጠቅሰው፤ በዘርፉ የመሪነት ሚና ለመወጣት የሚያስችል አቅም እንዳላት ተናግረዋል።
ኢንስቲትዩቱ የባዮቴክኖሎጂ ምርምሮችና ግኝቶችን ለማስተዋወቅ የተቀናጁ ተግባራትን እያከናወነ ነው
Dec 11, 2025 162
ሮቤ ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የባዮቴክኖሎጂ ምርምሮችና ግኝቶችን ለኅብረተሰቡ ለማስተዋወቅ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተቀናጁ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ገለጸ። የኢንስቲትዩቱ የግብርና ባዮ-ቴክኖሎጂ የደቡብ ምሥራቅ መድረክ (ኦፋብ ኢትዮጵያ) ከመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር የባለድርሻ አካላት ዐውደ ጥናት በባሌ ሮቤ አካሂዷል።   በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የግብርና ባዮ -ቴክኖሎጂ የኢትዮጵያ አስተባባሪ ታደሰ ዳባ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ በባዮ ቴክኖሎጂ ሳይንስ የግብርናው ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው። ቴክኖሎጂው በግብርናው መስክ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከፍተኛ እገዛ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።   ለአብነትም በባዮ ቴክኖሎጂ ሳይንስ በቆሎና የጥጥ ዝርያ ላይ እየተካሄዱ የሚገኙ ምርምሮች ተስፋ ሰጪ ውጤት ማምጣታቸውን አንስተዋል። የባዮቴክኖሎጂ ሳይንስ ጥቅምን በሕብረተሰቡ ዘንድ በአግባቡ እንዲታወቅና ተደራሽ እንዲሆን ተከታታይነት ያለው ግንዛቤ ለመፍጠር ከባለድርሻ አካላት ጋር መሰራቱን አመልክተዋል። የባዮ ቴክኖሎጂ ሳይንስ በተለይ የግብርናው ምርታማነት ላይ ማነቆ የሆኑ የሰብል በሽታዎች፣ አረምና ሌሎች ችግሮችን ለማቃለል የሚያግዝ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት መሪ ተመራማሪ ተስፋዬ ዲሳሳ (ዶ/ር) ናቸው።   በሀገሪቱ ባለፉት ዓመታት በቆሎን በማዳቀል ዘርፍ የተካሄዱ የምርምር ሥራዎች በሽታን የሚቋቋምና ምርታማነትን የሚያሻሽል ዘር መገኘቱን አንስተዋል። የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ፣ ምርምርና የቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት በዛብህ ወንድሙ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ሥራ በተጓዳኝ ችግር ፈቺ ምርምሮችን እያካሄደ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   ዩኒቨርሲቲው በተለይ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የተሻሻሉና የምርጥ ዝርያዎችንና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በምርምር ተደራሽ ማድረጉን ጠቅሰዋል። የተካሄደው መድረክም የተገኘውን ውጤት ለማሳደግ ጉልህ ድርሻ እንደሚኖረው አንስተዋል። የባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ በተካሄደው የባዮቴክኖሎጂ ዘርፍ መድረክ ላይ የምርምር ውጤቶችና የዘርፉን እምቅ አቅም ለኅብረተሰቡ ለማስተዋወቅ የሚረዱ ሰነዶች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
አውደ ጥናቱ ለኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ኃይል ልማት ቀጣይ ስራዎች መደላድል የሚሆን ግንዛቤ ተፈጥሮበታል
Dec 11, 2025 88
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦አውደ ጥናቱ ለኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ኃይል ልማት ቀጣይ ስራዎች መደላድል የሚሆን ግንዛቤ የተፈጠረበት መሆኑን የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ገለጸ። የመጀመሪያው ብሔራዊ የኒውክሊየር ኃይል መርሃ ግብር ሚና እና ኃላፊነት የተቋም ትግበራ አውደ ጥናት ምክክር መድረክ ዛሬ በአዲስ አበባ ተካሂዷል።   የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ተሊላ በዚሁ ወቅት፥ የኒውክሊየር ኃይል ለኢነርጂ፣ ለግብርና፣ ለጤና እንዲሁም ለኢንዱስትሪ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ገለጸዋል። የዚህ ኃይል አጠቃቀም በዓለም አቀፍ ሕግ የሚመራ መሆኑን ገልጸው ሀገራት ሊከተሏቸወ የሚገቡ ቅደም ተከተሎች መኖራቸውን ጠቁመዋል። በአውደ ጥናቱ በሀገር ውስጥ ያሉ ባለድርሻ አካላት እና የሚመለከታቸው ሌሎች ተቋማት መሳተፋቸውንና ግንዛቤ መፈጠሩን ተናግረዋል። የኒውክሊየር ፕሮግራሙ ሀገራዊ ፕሮጀከት በመሆኑ ህብረተሰቡ ለስኬቱ የሚጠበቅበትን ሚና እንዲወጣ ማስቻል ላይ ውይይቶች መደረጋቸውን ጠቁመዋል። በአውደ ጥናቱ በዓለም አቀፍ የሕግ ማእቀፎች እና ሊከናወኑ በሚገባቸው ስራዎች ላይ ውይይት መደረጉንም አመላክተዋል። የተቋማት አቅም እና የሰው ኃይል ግንባታ ሌላኛው በአውደ ጥናቱ በስፋት የተዳሰሰ መሆኑን ጠቁመዋል።   አውደጥናቱ በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት ቀጣይ ስራዎች መደላድል የሚሆን ግንዛቤ የተፈጠረበት መሆኑን ገልጸዋል። በአውደ ጥናቱ ከተሳተፉት መካከል የውመን ኢን ኒውክሊየር ኢትዮጵያ ፕሬዝደንት አበባ ጌጡ፤ አውደ ጥናቱ በቂ ግንዛቤ ያገኙበት መሆኑን ገልጸዋል።   በተለይም የዓለም አቀፉ አቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ባስቀመጣቸው አቅጣጫዎች ላይ ግንዛቤ ማግኘታቸውን ነው የገለጹት። በቀጣይም በፕሮግራሙ ላይ የሴቶች አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንዲሆን በስልጠና እንዲሁም በተለያዩ አውደ ጥናቶች የማብቃት ስራ እንደሚሰራ አስታውቀዋል። በአውደ ጥናቱ ጥልቅ እውቀት ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ በኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ባለስልጣን የጨረራና ኒውክሊየር ቴክኖሎጂ የማሳወቅ እና ፈቃድ አሰጣጥ መሪ ስራ አስፈጻሚ ስሩር ከድር ናቸው። ተጨማሪ እውቀት በመፍጠር በዘርፉ የተሰማሩትን ለበለጠ ስራ የሚያነሳሳ መሆኑን ተናግረዋል።
ፋይዳ መታወቂያ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው -ተቋማት
Dec 11, 2025 146
ሐረር፤ ታህሳስ 2/2018 (ኢዜአ) ፡- ፋይዳ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን በሐረሪ ክልል የሚገኙ የተለያዩ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ገለጹ። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ እየተከናወኑ ከሚገኙ ተግባራት መካከል የመንግስት የአገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታላይዝ ማድረግ አንዱ ነው። ለዚህም ይረዳ ዘንድ ማንኛውም አገልግሎት ፈላጊ ዜጋ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያን እንዲይዝ መንግስት የተለያዩ አማራጮችን መዘርጋቱ የዚሁ ጥረት አካል ነው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የሐረሪ ክልል አገልግሎት ሰጪ ተቋማት፤ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በሐረሪ ክልል ጠቅላይ ዐቃቢ ህግ የውልና ማስረጃ ምዝገባ ጽሕፈት ቤት ባለሙያ አቶ ዘኪ አብዱልማሊክ ፤ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተግባራዊ መደረጉ በተለይም ከዚህ በፊት በመታወቂያ ረገድ ይስተዋል የነበረው ማጭበርበር ችግር ማቃለሉን ገልጸዋል። ፋይዳ ከሲስተም ጋር የተሳሰረ በመሆኑ አንድ ሰው በአንድ ማንነትና በአንድ መታወቂያብቻ እንዲገለገል አድርጓል፣ የነበሩ ብልሹ አሠራሮችንም ሙሉ በሙሉ እንዳሰቀረ ተናግረዋል። የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ሁሉንም ዜጎች ተደራሽ ያደረገ ነው ያሉት ደግሞ በሐረሪ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል ኢትዮ- ፖስታ በሚሰጠው አገልግሎት የካውንተር ባለሙያ አቶ አብዲሳ ተካ ናቸው። በተጨማሪም ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ ለግለሰብም ሆነ ለሀገር ደሕንነት የጎላ ፋይዳ እንዳለውና እንደ ሀገር ለተጀመረው የዲጂታላይዜሽን ሥራዎች አንዱ ማሳያ መሆኑንም አክለዋል። ሌላው በሐረሪ መሶብ የአንድ ማዕከል ኢትዮ-ፖስታ በሚሰጠው አገልግሎት የካውንተር ባለሙያ ዮሐንስ እስቂያስ በበኩላቸው፤ ፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ተቋማት ያለ ልዩነት አገልግሎት እንዲሰጡ ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ሲል ተናግረዋል። በአገልግሎት ሰጪ እና ተቀባዩ መካከልም መተማመን እንዲፈጠር ያስቻለ ስለመሆኑም አንስተዋል። የሐረሪ ክልል ወሳኝ ኩነት ምዝገባ ኤጀንሲ ኃላፊና የፋይዳ ብሔራዊ መታወቂያ አስተባባሪ አቶ አርሰላን አብዲ ፤ በክልሉ እስካሁን 263ሺህ ዜጎች የፋይዳ መታወቂያ ተመዝግበው መውሰዳቸውንና ይህም ከእቅዱ በላይ ማሳካት መቻሉን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በክልሉ የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ያልወሰዱ ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም አክለዋል። የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም እንደ ሀገር ለተጀመሩ የዲጂታላይዜሽን፣ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና ዲጂታል ኢኮኖሚ ስርዓት ግንባታ ፋይዳው የጎላ መሆኑን አስረድተዋል። የሀገር እና ዜጎችን ደሕንነትን በማስጠበቅ ረገድ ጉልህ አአስተዋጽኦ አለው ያሉት ሃላፊው፤ ዜጎች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ መያዝ እንደሚጠቅማቸው በመረዳት የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል።  
የኢትዮጵያ የዲጂታል ክፍያ ስርዓት የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር በምሳሌነት የሚወሰድ ነው
Dec 11, 2025 98
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የዲጂታል ክፍያ ስርዓት የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር በምሳሌነት የሚወሰድ መሆኑን የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ዋና ጸኃፊ ዋምኬሌ ሜኔ ገለጹ፡፡ የአፍሪካ ሀገራትን የዕርስ በእርስ የንግድ ልውውጥ ለማሳለጥ የጋራ መገበያያ ገንዘብን ሥራ ላይ ማዋል እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል። ሁለተኛው የኢትዮጵያ የዲጂታል ክፍያ ዓመታዊ ጉበዔ ተካሂዷል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ዋና ጸኃፊ ዋምኬሌ ሜኔ በጉባዔው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በአፍሪካ በየዓመቱ የሚፈጸመውን የአምስት ቢሊዮን ዶላር የእርስ በእርስ የንግድ ልውውጥ በማሳለጥም የአህጉሪቱን የጋራ መገበያያ ገንዘብ ግብ ለማሳካት ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አስረድተዋል። የአህጉሪቱ የንግድ ልውውጥ በሶስተኛ ወገን ገንዘብ ይፈጸማል ያሉት ዋና ጸኃፊው፤ ይህም አፍሪካውያን ለአላስፈላጊ ወጪ እንዲጋለጡ እያደረጋቸው መሆኑን ገልጸዋል። የአፍሪካ ሀገራትን የዕርስ በዕርስ የንግድ ልውውጥ ወጪ ቆጣቢ፣ ዘመናዊና ፈጣን ለማድረግም አህጉራዊ የጋራ መጠቀሚያ ገንዘብን በሥራ ላይ ማዋል እንደሚገባ አስረድተዋል። በአህጉሪቱ የንግድ ልውውጥም ሀገራት በየራሳቸው ገንዘብ ግብይት የሚፈጽሙበትን ቀልጣፋ የአሰራር ሥርዓት መዘርጋት እንደሚገባም አብራርተዋል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናም የአፍሪካ ሀገራትን የንግድ ልውውጥ የሚያሳልጥ የአሰራር ሥርዓት ምክረ ሃሳቦችን በመፍጠር የድርሻውን እየተወጣ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ዋና ጸሃፊው ኢትዮጵያ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስኬታማ ስራ እየሰራች መሆኑንም ጠቁመዋል። በዲጂታል ክፍያ ስርዓት ፍትሐዊ የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር በምሳሌነት የሚወሰድ ሥራ እየሰራች መሆኗን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ መርሃ ግብር ለዲጂታል ሥርዓት ግንባታ ገንቢ ሚና እየተጫወተ ነው
Dec 11, 2025 94
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ መርሃ ግብር በህዝብና ተቋማት መካከል መተማመን በመፍጠር ለዲጂታል ሥርዓት ግንባታ ገንቢ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም አስታወቀ። የፕሮግራሙን ተቋማዊ አሰራርና ውጤታማነት ለማሳደግ የኢትዮጵያ ዲጂታል መታወቂያ በአዋጅ 1284/2015 በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጸድቆ ወደ ስራ መግባቱ ይታወቃል። አዋጁ ነዋሪዎች የመታወቅ መብታቸው እንዲረጋገጥ፣ ሌሎች መብቶቻቸውን የመጠቀም እድላቸውን ለማስፋት፤ በአገልግሎት ሰጭና ተቀባይ መካከል በሚኖር ግንኙነት እምነት እንዲዳብር፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ ግልጽነት፣ ተጠያቂነትና የተሳለጠ አሰራር ለመዘርጋት ያለመ ነው።   በብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የባለድርሻ አካላትና የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ሳሚናስ ሰይፉ ለኢዜአ እንደተናገሩት ዲጂታል ኢትዮጵያን በማሳለጥ ማጭበርበርን ከማስቀረት በተጨማሪ በህዝብና በተቋማት መካከል መተማመንን ለመፍጠር ዲጂታል መታወቂያ ጉልህ ሚና አለው። የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ አጀንዳና በዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ 2030 ውስጥ አንዱና ዋናው አስቻይ ምሰሶ መሆኑን ተናግረዋል። ለተለያዩ ዘርፎች አገልግሎት ለመስጠት አስቻይ ሁኔታን መፍጠር፤ ተደራሽነትን ማረጋገጥ እና ለዲጂታል የህዝብ መሰረተ ልማት መሰረት በመጣል በኢትዮጵያ ዲጂታላይዜሽንን ለማሳካት ጉልህ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። እስካሁን የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ያደረጉ ሰዎች ቁጥር 29 ሚሊየን መድረሱንም ጠቅሰዋል። በፕሮግራሙ የተቀመጠውን ቅድመ ሁኔታ ለሚያሟሉ ነዋሪዎች ባለ 12 አሃዝ ልዩ የፋይዳ መለያ ቁጥር እየተሰጠ እንደሚገኝና ይህ መለያ ቁጥር ያላቸው ሰዎች የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ተደርገው እንደሚቆጠሩ አስረድተዋል። በምዝገባ ሂደቱ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ህዝቡ በንቃት እንዲሳተፍን ጥሪ አቅርበዋል። የዲጂታል መታወቂያ ከተቋማት ጋር መተሳሰሩ የአገልግሎቱን ተጠቃሚ ቁጥር ለማሳደግ ፋይዳ እንዳለው አመልክተዋል።
በኦሮሚያ ክልል ከ900 ሺህ በላይ ዜጎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ወስደዋል
Dec 11, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል 956 ሺህ ዜጎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸውን የክልሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን አስታወቀ። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ እየተከናወኑ ከሚገኙ ተግባራት መካከል የመንግስት የአገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታላይዝ ማድረግ አንዱ ነው። ለዚህም ይረዳ ዘንድ ከመደበኛው የቴክኖሎጂ ትምህርቶች በተጨማሪ የኢትዮ-ኮደርስ እና የመሳሰሉ የበየነ መረብ የክህሎት ስልጠናዎችን መንግስት እንደ አማራጭ ለዜጎች ምቹ ማድረጉ የዚሁ ጥረት አካል ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በተጀመረውና ለ5 ሚሊዮን ዜጎች የተመቻቸው የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና በሁሉም ክልሎች በተለያዩ ዙሮች እየተሰጠ ይገኛል። በኦሮሚያ ክልልም ስልጠናው ከተጀመረ ወዲህ ከ900 ሺህ በላይ ዜጎች የእድሉ ተጠቃሚ በመሆን በርካቶቹ በዘርፉ ሥራ እስከ መፍጠር መድረሳቸው ተገልጿል። የክልሉ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ጅማ ቱሉ ለኢዜአ እንደተናገሩት በክልሉ የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠናው ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተለያዩ ስራዎች ተሰርተዋል። የስልጠናው ዓላማ ዜጎች በዲጂታል ዘርፍ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ከማድረግ ባለፈ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚያግዛቸው ጠቁመዋል። በተጨማሪም ስልጠናው ተማሪዎች ከቴክኖሎጂ ጋር ያላቸው ግንኙነት የጠበቀ እንዲሆን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ሲሆን ለስራ ፈላጊዎች ደግሞ እድላቸውን የሚያሰፋ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና እቅዱን ለማሳካት የግንዛቤ ፈጠራ፣ ቤተ ሙከራዎች የማዘጋጀት፣ ኮምፒዩተሮችና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን የማሟላት እንዲሁም የስልጠና ማዕከላትንና ሌሎችንም የማመቻቸት ስራዎች በሰፊው መሰራታቸውን ገልጸዋል። በክልሉ ዞኖችና ከተሞች ለመንግስት ሰራተኞች፣ ነጋዴዎች፣ ለአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች፣ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች የተመረቁ ተማሪዎች በስልጠናው በንቃት እየተሳተፉ ይገኛሉ ብለዋል። በአጠቃላይ በክልሉ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዜጎችን የስልጠናው ተጠቃሚ ለማድረግ የታቀደ ሲሆን እስካሁን 956 ሺህ ዜጎች ስልጠናውን መውሰዳቸውን ገልጸዋል። በብሔራዊ መታወቂያ የምዝገባ ስራ ላይ በርካታ ሰልጣኞች በቀጥታ ተሳታፊ በመሆን የስራ እድል ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኙም አብራርተዋል። በተያዘው በጀት አመት በክልሉ በኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና የተቀመጠውን ዕቅድ ለማሳካት ርብርቡ እንደሚቀጥልም ኢንጂነር ጅማ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በዲጂታል ክፍያ ያስመዘገበችው አስደናቂ ስኬት ተጨማሪ ግቦችን ለማሳካት መሠረት የሚሆኑ ናቸው
Dec 10, 2025 151
አዲስ አበባ፤ታኅሣስ 1/2018(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በዲጂታል ክፍያ ያስመዘገበችው አስደናቂ ስኬት ተጨማሪ ግቦችን ለማሳካት መሠረት የሚሆኑ ናቸው ሲሉ የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ። ሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ በስኬት ተጠናቋል።   በጉባኤው ማጠናቀቂያ ንግግር ያደረጉት የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በዲጂታል ክፍያ ዘርፍ እያስመዘገበች ያለችው ዕድገት አስደናቂ ነው። አሁን ላይ አብዛኛው ዜጋ ከፍተኛ መጠን ያለው ጥሬ ገንዘብ መያዝ አቁሟል ያሉት ገዥው፤ ኢትዮጵያውያን የዲጂታላይዜሽን እና የዳታ ሽግግርን በፍጥነት እየተላመዱ እንደሚገኙም አስረድተዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት በተዘረጋው የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት በየዓመቱ ከ18 ነጥብ 5 ትሪሊዮን ብር በላይ የገንዘብ ዝውውር መከናወኑን ተናግረዋል። ይህን የገንዘብ ዝውውር በጥሬ ገንዘብ ቢከናወን ከፍተኛ ወጪና መጨናነቅ ይፈጥር እንደነበር ጠቁመው፤ ይህ ስኬት ከጥቂት ዓመታት በፊት ፈጽሞ የማይታሰብ እንደነበር ጠቅሰዋል። የመሠረተ ልማትን ለማስፋፋት የተሰጠው ትኩረት ዋነኛ የስኬቱ መገለጫ መሆኑን ገልጸዋል። መንግሥትን ወደ ዲጂታል ግብይት እና የገንዘብ ዝውውር አገልግሎት ለማሸጋገር የሰጠው ትኩረት ለተመዘገበው ውጤት ትልቅ እርምጃ መሆኑን ጠቅሰው፤ በትክክል የታሰበበት፣ በጥንቃቄ የተቀረጸና ተግባራዊ የተደረገ የስትራቴጂ ውጤት ስለመሆኑም ጠቁመዋል። እስካሁን የተገኘውን ውጤት ይበልጥ ለማጎልበት እንደሚሰራ ጠቁመው፤ ውጤቱ የሚያዘናጋ ሳይሆን መስፈንጠሪያ ሊሆን እንደሚገባም ተናግረዋል። በቀጣይ የዲጂታል ባንኪንግ ተጠቃሚዎችን እምነት ለማሳደግ እና የሥርዓቱን ደኅንነት ይበልጥ ለማረጋገጥ እንደሚሰራ ጠቅሰው፤ በገጠርና በከተማ ያለውን የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ልዩነት ለመቀነስ ይሠራል ብለዋል። እንዲሁም የፈጠራ ሥራዎችን በበቂ ሀብት የመደገፍ ሥራዎች ወሳኝ በመሆናቸው በልዩ ትኩረት ይሠራል ብለዋል። ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በቁርጠኝነት ሠርታ ያስመዘገበቻቸው ትላልቅ ውጤቶች በቀጣዮቹ ዓመታት ለማሳካት ያስቀመጠቻቸውን ግቦች ለማሳካት ትልቅ መሠረት የሚሆኑ ናቸውም ብለዋል። ኢትዮጵያ የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን ለመገንባት ትክክለኛ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በመቅረፅ ትክክለኛውን እርምጃ መውሰዷንም ገልጸዋል። ሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ የመረጃ መሠረተ ልማትን ለማጠናከር፣ የዲጂታል ክፍያ እና ሰፋፊ የዲጂታል ስትራቴጂዎችን ለማስገንዘብ ሰፊ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የዲጂታል መሠረተ ልማቶችን ለማስፋፋት መንግስት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ለዚህም በርካታ ኢንቨስትመንት መከናወኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የዲጂታል ክፍያ ዘርፍ እንዲስፋፋ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይ ትኩረት ከሚሰጣቸው ተግባራት መካከል የመረጃ ሉዓላዊነት ጉዳይን አንስተዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በብዙ መልኩ ኢንቨስት እያደረገች እንደምትገኝም አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የዲጂታል ፋይናንስና የክፍያ ሥርዓት በፈጣን የዕድገት ጎዳና ላይ እንደምትገኝም ጠቁመዋል። ከ2026 -2030 የሚተገበረው ብሔራዊ የዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ በሁለተኛው የኢትዮጵያ ዲጂታል ክፍያ ጉባኤ መክፈቻ ላይ ይፋ መደረጉን ይታወቃል።  
የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኅይል ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት ያለመ ነው  
Dec 10, 2025 170
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር ከኢኮኖሚው ጋር አብሮ እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኅይል ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት ያለመ መሆኑን የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ተሊላ ገለጹ። የመጀመሪያው ብሔራዊ የኒውክሊየር ኃይል መርሃ ግብር ሚና እና ኃላፊነት የተቋም ትግበራ አውደ ጥናት የምክክር መድረክ ሁለተኛ ቀን ቀጥሏል።   የኢትዮጵያ የኒውክሊየር ኅይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ተሊላ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኒውክሊየር ኃይል ተፈጥሮ ለአንድ ሀገር ዘላቂ ልማት እና እድገት ወሳኝ ነው። ኢትዮጵያ የምትከተለው አረንጓዴ ኢኮኖሚ መሆኑን ገልጸው፤ የኢንዱስትሪዎቿ ቁጥር እና ዓይነት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መሆኑን ገልጸው፤ ይህ ወደ ኋላ እንዳይመለስ የኃይል ምንጭን አስቀድሞ ማዘጋጀት ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሊየር ልማት መርሃ ግብር እያደገ የመጣውን የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎት ምላሽ መስጠት የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ኒውክሊየር ኃይል ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አብዱረዛቅ ኡመር በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ከአካባቢ ጥበቃ ጋር የተስማማ በቂ እና አስተማማኝ ኃይል ለኢንዱስትሪዎች በማቅረብ ወደ ፊት መራመድ እንደምትፈልግ ተናግረዋል።   የኢትዮጵያን ሰላማዊ የኒውክሌር ኃይል አማራጭ የሀገሪቱን የልማት ትልሞች የሚያሳካ መሆኑን ጠቁመዋል። በመካሄድ ላይ ባለው ዓውደ ጥናት የተለያዩ ሀገራት ልምድ እና ተሞክሮዎች ቀርበው ውይይት እየተደረገባቸው መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም አንድ ሰላማዊ የኒውክሊየር መሰረተ ልማት ለማቋቋም መከናወን ባለባቸው ተግባራት ላይ ግንዛቤ እየተፈጠረ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም