ሳይንስና ቴክኖሎጂ
አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በመንግሥት አሰራሮች፣ በማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ በንግድ፣ በትምህርት እና በሌሎች መስኮች መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ ይገኛል
Jul 26, 2024 234
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በመንግሥት አሰራሮች፣ በማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ በንግድ፣ በትምህርት እና ሌሎችም መስኮች መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ አቶ ተመስገን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ ዙሪያ የተዘጋጀውን ዐውደ ጥናት ተካፍለናል ብለዋል፡፡ ዐውደ ጥናቱ ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች የተገኙበት እና በቢግ ዳታ፣ ጄኔሬቲቭ ኤ.አይ፣ በአመራሮች ውሳኔ አሰጣጥ፣ በፖሊሲ እና ሕዝብን በማገልገል ሂደት ውስጥ ቴክኖሎጂውን በመጠቀም ውጤታማነትን እንዴት ማሳደግ እንደሚቻል ግንዛቤ የተወሰደበት ነበርም ብለዋል በመልዕክታቸው፡፡   አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዛሬ ላይ በሁሉም መስኮች አገልግሎት ላይ እየዋለ ነው ሲሉም ገልጸዋል፡፡ በዚህም በመንግሥት አሰራሮች፣ በማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ በንግድ፣ በትምህርት እና ሌሎችም መስኮች መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ ይገኛል ብለዋል፡፡ እኛም በዚህ ዘርፍ በርትተን በመስራት እና የሕዝባችንን ችግሮች መፍታት የሚችሉ የተለያዩ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሥርዓቶችን በማበልፀግ መጠቀም ይገባናል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ የቴክኖሎጂውን ሙሉ አቅም ተገንዝቦ ወደ ተግባር የሚለውጥ የሰው ኃይል መገንባት ደግሞ ሌላኛው ቁልፍ ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ አንጻር እንደነዚህ ያሉ ዐውደ ጥናቶች ጉልህ ሚና እንዳለቸው እናምናለን ሲሉም ገልጸዋል፡፡ በወዳጅ ሀገር የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ተቀማጭነቱን ባደረገው ፕሪሳይት በተባለው ተቋም ለሦስት ቀናት የተዘጋጀው ዐውደ ጥናት በዘርፉ ያቀድነውን ወደ መሬት ለማውረድ ከሚሰጠው አቅጣጫ አንጻር ስኬታማ ነበርም ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፡፡
ብሔራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲን ማስተግበሪያ ስትራቴጂና ማስፈጸሚያ ፕሮግራሞች ተዘጋጅተዋል
Jul 26, 2024 131
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ ብሔራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲን መተግበር የሚያስችሉ ስትራቴጂና ማስፈጸሚያ ፕሮግራሞች መዘጋጀታቸውን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ገለጸ፡፡ የተለያዩ የዓለም ሀገራት አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን ከመዝናኛና የመገልገያ ዘዴዎች እስከ ብሔራዊ ደህንነትና መረጃ አገልግሎት ላሉ ቁልፍ ጉዳዮች ጭምር ጥቅም ላይ እያዋሉት ነው፡፡ ኢትዮጵያም ቴክኖሎጂውን ለማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ አገልግሎት ለማዋል፣ ፀጥታና ደህንነት ለማስጠበቅና በዘርፉ ተወዳዳሪ አቅም ለመፍጠር በርካታ ስራዎች ተከናውነዋል፡፡ በተለይም ከለውጡ በኋላ ዘርፉን የሚመራ ተቋም በመመስረት የኢትዮጵያን ትልሞች ለማሳካት እየተሰራ ነው። ከዚህም ባለፈ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ሰኔ 20 ቀን 2016 ዓ.ም ባካሄደው 37ኛ መደበኛ ስብሰባ ብሔራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲ ስራ ላይ እንዲውል ወስኗል፡፡ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር ኢ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ፖሊሲውን ለማዘጋጀት ከሁለት ዓመት በላይ ጊዜ ወስዷል፡፡ ፖሊሲው መንግስት በዘርፉ ሊደርስበት የፈለገውን ግብ ማሳካት እንዲችል የተለያዩ ባለሙያዎችን በማሳተፍና የሀገራትን ልምድ በመቀመር ስለመዘጋጀቱም ነው ያብራሩት። በርካታ ሀገራት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲ እንደሌላቸው የጠቀሱት ዋና ዳይሬክተሩ የኢትዮጵያ መንግስት ፖሊሲው ወደ ስራ እንዲገባ መወሰኑ ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ ፖሊሲው ማንኛውም በውጭ የሚኖር ኢትዮጵያዊ ወደ ሀገሩ በመምጣት በዘርፉ በመሰማራት ራሱንና ሀገሩን በቴክኖሎጂ ማሳደግ የሚችልበትን እድል እንደሚፈጥርም አንስተዋል። ብሔራዊ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፖሊሲን በፍጥነት ሥራ ላይ ለማዋል የሚያግዙ ስትራቴጂና የማስፈጸሚያ ፕሮግራሞች መዘጋጀታቸውንም ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።    
ቻይና በቴክኖሎጂና በወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ዘርፍ የኢትዮጵያ ወጣቶችን ለማብቃት አስፈላጊውን እገዛ እንደምታደርግ ገለጸች
Jul 26, 2024 130
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ ቻይና በቴክኖሎጂና በወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ዘርፍ የኢትዮጵያ ወጣቶችን ለማብቃት አስፈላጊውን እገዛ እንደምታደርግ ገልጻለች። የኢትዮጵያ ወጣቶች ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ፉአድ ገና ከብሪክስ የወጣቶች ጉባኤ ጎን ለጎን ከቻይና የወጣቶች ፌዴሬሽን ምክትል ፕሬዝዳንት ጎንግ ጂንሎንግ ጋር ተወያይተዋል፡፡ መሪዎቹ በቻይና አፍሪካ የትብብር ማዕቀፍ ስር በትምህርት ፤ በስራ ፈጠራ፤ በወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎትና በቴክኖሎጂ ሽግግር ዙሪያ በጋራ ለመስራት ተስማምተዋል፡፡   በቻይና በየዓመቱ በሚካሄደው የአለም ወጣቶች ዴቨሎፕመንት ፎረም ላይ ኢትዮጵያውያን ወጣቶች በስፋት የሚሳተፉበትን እድል ለማመቻቸት በሚያስችሉ ነጥቦች ላይም ተወያይተዋል፡፡ የሁለቱን ሀገራት የወጣት ለወጣት ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋር እንደሚሰሩ ያረጋገጡት መሪዎቹ በኢትዮጵያ የቻይንኛ ቋንቋ ማስተማሪያ ማዕከላትን ለማስፋፋትም ከስምምነት ደርሰዋል፡፡ ኢትዮጵያ በቻይና የቤልት ኤንድ ሮድ ኢኒሼቲቭ ማዕቀፍ ስር ተጠቃሚ የምትሆንበትን አማራጭ ለማስፋትም አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ ምክትል ፕሬዝዳንት ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ-ቻይና ወጣቶች ጉባኤን በ2025 እንደምታስተናግድ የወጣቶች ምክር ቤት በማህበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል።
ኢትዮጵያና ቻይና  በሳይንስና ቴክኖሎጂ ያላቸውን ትብብር አጠናክረው እንደሚቀጥሉ  ገለፁ
Jul 25, 2024 171
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 18/2016 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያና ቻይና በሳይንስና ቴክኖሎጂ ልማት ያላቸውን ትብብር ይበልጥ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገለፁ። የኢትዮጵያና ቻይና ሦስተኛው የሳይንስና ቴክኖሎጂ የጋራ ኮሚቴ ስብሰባ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። ያለፉት ዓመታት የሳይንስና ቴክኖሎጂ የትብብር ማዕቀፎችን በመገምገም በቀጣይ አምስት ዓመታት በአዳዲስ ዘርፎች ላይ አብሮ ለመስራትም የመግባቢያ ስምምነት ተፈርሟል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በንግግራቸው፥ ኢትዮጵያ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን እውን የማድረግ ጉዞን መጀመሯን ገልጸው፥ ለውጤታማነቱም ምቹ ምህዳር ተፈጥሯል ብለዋል።   ለሳይንስ፣ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ በተሰጠው ትኩረት በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስኮች አበረታች ውጤቶች እየተመዘገቡ ስለመሆኑም አንስተዋል። የዜጎችን ህይወት ለማሻሻልና የሀገርን እድገት ለማፋጠን ቴክኖሎጂ ወሳኝ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፥ ለስኬቱም ከአጋር አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ ነው ብለዋል። በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ያላቸው ኢትዮጵያና ቻይና በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍም በትብብር እየሰሩ እንደሆነ ጠቅሰዋል።   የሀገራቱ ትብብር ለኢትዮጵያ የዲጅታል ሽግግር መሳካት የላቀ ሚና እንዳለው በማንሳት፥ በቀጣይም የቴክኖሎጂ ፈጠራን በሚያሳድጉ የትምህርትና ስልጠናና ሌሎች ትብብሮች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። ዛሬ የተፈረመው የመግባቢያ ስምምነትም ባለሙያዎች በሳይንስና ቴክኖሎጂ የእውቀት ሽግግርና የልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉ እንዲሁም በዘርፉ የጋራ የጥናትና ምርምሮችን ለማድረግ ያስችላል ነው ያሉት። የቻይና ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሊን ዢን በበኩላቸው የዛሬው መድረክ የሀገራቱን የፈጠራ ስራ ትብብር ለማጠናከር የሚያግዝ እንደሆነ ተናግረዋል። ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላትን ትብብር ይበልጥ አጠናክራ እንደምትቀጥልም አረጋግጠዋል።    
በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በላቀ ክህሎት ሀገራቸውን የሚያስጠሩ በርካታ ባለተሰጥኦ ወጣቶች እየተፈጠሩ ነው
Jul 25, 2024 124
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2016(ኢዜአ)፦ በሰው ሰራሽ አስተውሎት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ሀገራቸውን የሚያስጠሩ በርካታ ባለተሰጥኦ ወጣቶች እየተፈጠሩ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር) ገለጹ፡፡ ኢንስቲትዩቱ የታዳጊ ወጣቶችን የቴክኖሎጂና ፈጠራ አቅም ለማሳደግ ከመደበኛ ትምህርታቸው ጎን ለጎን የክረምት ሥልጠና እየሰጠ ይገኛል። በዘንድሮው ዓመትም ለሶስተኛ ዙር የሰው ሰራሽ አስተውሎት የክረምት ሥልጠና ከመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች 200 ተማሪዎችን አወዳድሮ ለይቷል፡፡ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር ኢ/ር)፤ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ በትኩረት መስራት ለሀገር እድገት መሰረት መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ኢንስቲትዩቱ ለዘርፉ እድገት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው ለተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው ባሻገር አዳዲስ እውቀት የሚያገኙበት የተደራጀ የክረምት ስልጠና እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመጀመሪያውና ሁለተኛው ዙር ሥልጠና ተሰጥኦዎቻቸውን ወደ ውጤት በመቀየር ከግል ተቋማት ጋር በትብብር መሥራት የሚችሉበት እድል ስለመፈጠሩም አስታውሰዋል። በመሆኑም የክረምት የታዳጊዎች ስልጠና ኢትዮጵያን በምርምርና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ከፍ የሚያደርጉ ዓለምን የሚለውጡ ወጣቶች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የክረምት የታዳጊዎች ሥልጠና ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂና ፈጠራ ዘርፍ ዓለምን የሚያስጠሩ ባለተሰጥኦ ወጣቶች ባለቤት መሆኗን አሳይቶናል ነው ያሉት፡፡ ወጣቶች የላቀ እውቀትና ሀሳብ እንዳላቸው ገልጸው፤ አቅማቸውን አውጥተው መጠቀም የሚችሉበትን እድል ማመቻቸት ደግሞ የእኛ ድርሻ ነው ብለዋል፡፡ በመሆኑም ለሥልጠናው በዘርፉ የካበተ ልምድ ያላቸው መምህራን፣ ምቹ የቴክኖሎጂ መሳሪያዎች፣ ቤተ ሙከራዎች እና መሰል ግብዓቶች የተሟሉለት ማዕከል መገንባቱን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያና የቻይና የሳይንስና ቴክኖሎጂ የትብብር መድረክ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው
Jul 25, 2024 125
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 18/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያና የቻይና ሦስተኛው የሳይንስና ቴክኖሎጂ የትብብር መድረክ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። በጉባዔው የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፣ የቻይና ሳይንስና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሊበ ዢን እና ሌሎችም ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንገዶች ተገኝተዋል። በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን እውን ለማድረግ በሚያስችል ጥረት ውስጥ መሆኗን ገልጸዋል። የኢትዮጵያና ቻይና ዲፕሎማሲ በጠንካራ ግንኙነት መቀጠሉን ጠቅሰው፤ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ድጋፍና ትብብሩም ለድጅታል ትራንስፎርሜሸን እቅድ መሳካት የላቀ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል። ሁለቱ አገሮች በኢንቨስትመንት፣ ግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ በመሠረተ-ልማትና ሌሎችም መስኮች ተቀራርበው መስራታቸውን አጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። የዛሬው መድረክም የዘርፉ ባለሙያዎች በሳይንስና ቴክኖሎጂ የእውቀት ሽግግርና የልምድ ልውውጥ የሚያደርጉበት ይሆናል ነው ያሉት።  
የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ  ከስራ ፈጠራ ባሻገር ለአገልግሎት ዘርፍ ኢንቨስትመንት መጎልበት ሚናው የጎላ ነው
Jul 23, 2024 498
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ከስራ ፈጠራ ባሻገር ለአገልግሎት ዘርፍ ኢንቨስትመንት መጎልበት ሚናው የጎላ መሆኑ ተገለጸ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሼቲቭን በዛሬው ዕለት በይፋ አስጀምረዋል፡፡ ኢኒሼቲቩ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስና የኢትዮጵያ መንግስታት የሚተገበር ሲሆን፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያሉ 5 ሚሊዮን ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና የሚወስዱበት ነው፡፡ ስልጠናውም በዋናነት በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ ከኢኒሼቲቩ ማስጀመሪያው በተጓዳኝ የዲጂታል ኢትዮጵያ ጉዞ ላይ ትኩረት ያደረገ የፓናል ውይይት ተካሂዷል፡፡ በውይይቱ ከተሳተፉት መካከል የትምህርት ሚኒስትሩ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ፤ ኢኒሼቲቩ የትምህርት ዘርፉ ብቁ ትውልድ ለመገንባት በሚያከናውነው ስራ ላይ ከፍተኛ አበርክቶ እንዳለው አብራርተዋል፡፡   በተለይ ትውልዱ በንድፈ ሃሳብ የሚያገኛቸውን እውቀቶች በቀላሉ ወደ ተግባር እንዲለውጥ ምቹ እድል በመፍጠር በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ያስችላል ነው ያሉት፡፡ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል በበኩላቸው ቴክኖሎጂ ከስራ ፈጠራ ጋር የሚተሳሰር ዘርፍ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡   የወጣቶችን ዲጂታል አቅም ለመገንባት የተሰጠው ትኩረት ደግሞ ግብርናን ጨምሮ የተለያዩ መስኮችን ለማዘመን የተያዘውን ውጥን እውን ለማድረግ እንደሚያግዝ ነው የተናገሩት፡፡ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ መንግስትን ወክለው በፓናሉ የተሳተፉት አብዱልአዚዝ አልጃዝሪ በኢትዮጵያ የዲጂታል ቴክኖሎጂን እውን በማደረግ ረገድ ከፍተኛ የሆነ የአመራር ቁርጠኝነት መኖሩን አንደታዘቡ ተናግረዋል፡፡   ይህ ደግሞ በኢኒሼቲቩ የተያዙ ግቦች እንዲሳኩ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ጠቁመዋል፡፡ ቴክኖሎጂ የዓለምን ነባራዊ ሁኔታ በእጅጉ እየቀየረ ስለመሆኑ አንስተው፤ ከዚህ አኳያ ለዘርፉ ቅድሚያ መስጠት ይገባል ብለዋል፡፡ የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ከ10 ዓመቱ መሪ የልማት አቅድ ጋር የሚጣጣም መሆኑን ያብራሩት ደግሞ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) ናቸው፡፡   በእቅዱ ላይ ዲጂታል ክህሎትን መሰረት ያደረገ የሰው ኃይል ልማት ትኩረት እንደተሰጠው ጠቅሰው፤ ኢኒሼቲቩም ይህን እውን በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሚና አለው ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል ኢኒሼቲቩ በኢትዮጵያ ክህሎት ያለው የሰው ሃይልን በመገንባት ትልልቅ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች በአገልግሎቱ ዘርፍ ኢንቨስት እንዲያደርጉ የሚያግዝ ነው ብለዋል፡፡ የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ኃይሌ (ዶ/ር) ዘመናዊና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥን እውን ማድረግ መንግስት እያከናወነ ያለው የሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያ አካል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡   ለዚህ ደግሞ የመንግስት ሰራተኞች ዲጂታል ክህሎት ማደግ እንዳለበት ጠቅሰው፤ ኢኒሼቲቩም የሲቪል ሰርቪስ ማሻሻያውን የሚያግዝ ስለመሆኑ አብራርተዋል፡፡  
የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ወጣቶች በዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ በንቃት እንዲሳተፉ የሚያደርግ ነው - በለጠ ሞላ (ዶ/ር)
Jul 23, 2024 243
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016 (ኢዜአ)፦የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ወጣቶች በዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ በንቃት እንዲሳተፉ የሚያደርግ መሆኑን የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሼቲቭን በዛሬው ዕለት በይፋ አስጀምረዋል፡፡ ኢኒሼቲቩ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስና ኢትዮጵያ መንግስታት የሚተገበር ሲሆን፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያሉ 5 ሚሊዮን ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና የሚወስዱበት ነው፡፡ ስልጠናውም በዋናነት በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ወሳኝ ከሆኑት መሰረቶች አንዱ የዲጂታል ስነ ምህዳሩን ማስፋት መሆኑን አንስተዋል፡፡ የዲጂታል ስነ ምህዳሩን ከሚያሰፉ ስራዎች መካከል ዋነኛው የክህሎት ግንባታ መሆኑን ገልጸው፤ በዘርፉ እውቀትና ክህሎት ያለው የሰው ሀይል ማፍራት ላይ በትኩረት እየተሰራ እንደሆነም ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ አኳያ የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ወጣቶች በዲጂታል ስነ ምህዳር ውስጥ በንቃት እንዲሳተፉ የሚያስችላቸውን ክህሎት የሚያገኙበት መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂው መስክ ወደ ፊት እንድትራመድ በር የሚከፍት መሆኑንም እንዲሁ፡፡ ኢኒሼቲቭ መንግስት ወጣቶች ለማብቃት፤ ፈጠራን ለማጎልበት እንዲሁም የዲጂታል አቅም ለመጠቀም ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህም ወጣቶች በዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ ንቁ ተሳታፊ እና አምራች እንዲሆኑ የሚያስችላቸውን ክህሎት የሚያገኙበት መሆኑን ገልጸዋል። አንድ ሰው የዲጂታል ክህሎት አለው የሚያስብለው ከቴክኖሎጂው ባሻገር ዘመኑን የሚዋጅ አስተሳሰብን ሲላበስ መሆኑን ጠቅሰው፤ በመሆኑም ወጣቶች ከቴክኖሎጂ በተጨማሪ ህሊናዊና ባህሪያዊ የሆኑ የዲጂታል ዘመን ስብዕናን መገንባት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ለኢኒሼቲቩ ስኬታማነት የፌደራል እና የክልል የመንግስት መዋቅሮች፤ የግሉ ዘርፍ የልማት አጋሮች እንዲሁም የሲቪል ማህበረሰብ እና ወላጆች የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል፡፡   የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አብዱላ ናስር፤ ኢኒሼቲቭ የኢትዮጵያና የተባበሩት አረብ ኢምሬትስ ያላቸውን አጋርነት ወደ አዲስ ምእራፍ የሚያሸጋግር መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም ሁለቱን አገራት በጋራ ተጠቃሚ በሚያደርጉ ሌሎች የትብብር መስኮች ለማስተሳሰር በትኩረት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል፡፡ በተያያዘ ዜናም የአስፈጻሚ አመራሮች ስልጠና መርሃ ግብር ይፋ ተደርጓል፡፡ ስልጠናው ኢትዮጵያና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች በትብብር የሚሰጡት ሲሆን፤ ከ15 የመንግስት ተቋማት የተወጣጡ አመራሮች ስልጠናውን የሚወስዱ ይሆናል፡፡ ስልጠናው ስድስት ወራት የሚወስድ ሲሆን፤ በኦንላይና አካል እንደሚሰጥ ተገልጿል፡፡  
ዲጂታል አቅምና ነገን የሚዋጅ አስተሳሰብ ያለው ትውልድ በመገንባት ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት የሚሆን ስራ እየተከናወነ ነው- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ 
Jul 23, 2024 231
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016 (ኢዜአ)፦ዲጂታል አቅምና ነገን የሚዋጅ አስተሳሰብ ያለው ትውልድ በመገንባት ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት የሚሆን ስራ እየተከናወነ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሸቲቭን በዛሬው ዕለት በይፋ አስጀምረዋል፡፡ ኢኒሸቲቩ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስና የኢትዮጵያ መንግስታት የሚተገበር ሲሆን፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያሉ 5 ሚሊዮን ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና የሚወስዱበት ነው፡፡ ስልጠናውም በዋናነት በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክኅሎት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ፤የተባበሩት አረብ ኤመሬትስ ፕሬዝዳንት ሸክ መሃመድ ቢን ዛይድ ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት ሁለቱ ሀገራት በተለያዩ መስኮች በጋራ ለመስራት ስምምነት መፈራረማቸውን አስታውሰዋል፡፡ ስልጠናውም የዚሁ ስምምነት አካል መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡   ኢትዮጵያ በአሳቢ ወጣት ዜጎቿ ተስፋ አላት ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የኢትዮጵያ ብልጽግና የሚረጋገጠው ዲጂታል አቅምና ነገን የሚዋጅ አስተሳሰብ ያለው ትውልድ መገንባት ሲቻል ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ አኳያ የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሸቲቭ ይህን ታሳቢ ያደረገ ስራ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በኢነሸቲቩ እድሉን የሚያገኙ ወጣቶች በትብብርና በመደመር እሳቤ በዘርፉ ኢትዮጵያን ወደ ታሻለ ምእራፍ ለማሸጋገር መስራት እንደሚጠበቅባቸውም አስገንዝበዋል፡፡ በቀጣይም ብቁ ትውልድን በመገንባት ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት የሚሆኑ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶችን ጨምሮ ከመካከለኛው ምስራቅ አገራት ጋር ያላትን ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር እየሰራች መሆኑንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ በተለይ ከተባበሩት ኤምሬቶች ጋር ትውልድን መገንባት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ጋር በቅርበት እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ በቀጣይም ትብብርን በማጠናከር የኢትዮጵያን ብልጽግና እውን ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል፡፡
ኮደርስ መርሃ ግብር አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክሂሎት የሚያስጨብጥ ነው
Jul 23, 2024 241
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦ ኮደርስ መርሃ ግብር አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክሂሎት የሚያስጨብጥ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የ''አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ’’ መርሃ ግብር በኢትዮጵያ እና በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ መንግሥታት የተጀመረ የዲጂታል ሥራ ክሂሎቶችን የማሳደጊያ የትብብር ፕሮጀክት እንደሆነም ተገልጿል። በማደግ ላይ ባለው ዲጂታል ኢኮኖሚ ከባቢ የመጪው ትውልድ ኢትዮጵያውያንን ለማብቃት ታልሞ የተጀመረ እንደሆነም ተመላክቷል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዛሬ በሳይንስ ሙዚየም አዲሱን መርሃግብር የዲጂታል እውቀትን ክፍተት ለማጥበብ የሚያስችል የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 አካል በማድረግ በይፋ ማስጀመራቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል። እ.ኤ.አ በ2026 መርሃግብሩ አምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክሂሎት የሚያስጨብጥ መሆኑንም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል።
የታዳጊዎች የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሥልጠና የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን የሚያደርጉ ወጣቶችን ለማፍራት መሰረት የሚጥል ነው
Jul 20, 2024 416
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 13/2016(ኢዜአ)፦የሰው ሰራሽ አስተውሎት የክረምት የታዳጊዎች ሥልጠና የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ማድረግ የሚችሉ ወጣቶችን ለማፍራት መሰረት እየጣለ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ገለጸ፡፡ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሶስተኛው ዙር የታዳጊዎች የክረምት ስልጠና ማስጀመሪያ መርኃ ግብር በሳይንስ ሙዚየም ተከናውኗል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገትና የኢኮኖሚ ሽግግር አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የማይተካ ሚና እንዳለው በመግለጽ በዘርፉ ላይ መስራት እንደሚገባ በተለያዩ መድረኮች ማንሳታቸው ይታወሳል።   በተለይም ለመጭው ዘመን ትውልድ የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በታዳጊዎችና ወጣቶች ላይ መልካም ዘር መዝራት እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ ተነጥላ መቀመጥ እንደማትችልና በዘርፉ እየተከናወነ ያለው ስራ አበረታች መሆኑንም መጠቆማቸው አይዘነጋም። የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) በስልጠናው ማስጀመሪያ መርሐግብር ላይ እንዳሉት፤ ለዘንድሮው ስልጠና ከ3 ሺህ በላይ ታዳጊዎች ተመዝግበው 200ዎቹ ተመርጠዋል። በዓለም ላይ በፍጥነት እያደገ የመጣውን የሰው ሰራሽ አስተውሎት የሚመጥን የሰው ሀይል ለማፍራት በታዳጊዎች ላይ መስራት ይገባል ብለዋል።   ለዚህም ኢንስቲትዩቱ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ምርምር በማድረግ የሀገራቸውን ችግር የሚፈቱና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን መስራት የሚችሉ ታዳጊዎችን እያሰለጠነ መሆኑን ገልጸዋል። ስልጠናው ችግር ፈቺ ምርምር በማድረግ በዘርፉ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብቱ ወጣቶችን ለማፍራት የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡ ኢንስቲትዩቱ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ከፍተኛ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ገልጸው፤ የክረምት ሰልጣኝ ታዳጊዎች ችግር ፈቺ ፕሮጀክቶችን ማፍለቅ እንዲችሉ አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ነው ያሉት። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኢንፎርሜሽን ሳይንስ ትምህርት ክፍል መምህርት ማርታ ይፍሩ (ዶ/ር)፤ በዚህ ዘመን ቴክኖሎጂ በእያንዳንዱ ቤት በቀላሉ የሚገኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡   ቴክኖሎጂ ተስፋም ስጋትም እንዳለው ገልጸው፤ ወጣቶች በእጃቸው ላይ ያለውን ቴክኖሎጂ በአግባቡ በመጠቀም ለሀገር ልማትና እድገት ሊያውሉት ይገባል ብለዋል፡፡ የቴክኖሎጂ ባለሙያው ሰለሞን ሙሉጌታ ካሳ፤ ሰው ሰራሽ አስተውሎት የሀገሪቱን ችግር የሚፈታ፣ ህይወትን የሚያቀል ቴክኖሎጂ መሆኑን ገልጿል፡፡ ሰው ሰራሽ አስተውሎት የዲጅታል ዘመን መዘውር፣ ታላቅ የቴክኖሎጂ አብዮት በመሆኑ ታዳጊዎች በጥንቃቄ ሊጠቀሙበት እንደሚገባ አሳስቧል፡፡ በመጀመሪያው እና በሁለተኛው ዙር የክረምት የታዳጊዎች ስልጠና ሰልጣኞች ተማሪ ይዲዲያ ታደሰ እና ዮሴፍ ልዑልሰገድ፤ በወሰዱት ስልጠና የቴክኖሎጂ አቅማቸውን ማሳደጋቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ኢንስቲትዩቱ በሰጣቸው ፕሮጀክት መሰረት ዘመናዊ የአይነ ስውራን ዘንግ እና ማንነታቸው ያልታወቀ ሰዎች ወደ ቤት ሲገቡ በእጅ ስልክ ምልክት የሚሰጥ የደህንነት መጠበቂያ ቴክኖሎጂ አበልጽገው ሥራ ላይ ማዋላቸውን ተናግረዋል፡፡  
የሰው ሰራሽ አስተውሎት የታዳጊዎች የክረምት መርሀ ግብር ስልጠና ተጀመረ
Jul 20, 2024 281
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 13/2016(ኢዜአ)፦ ሶስተኛው ዙር የሰው ሰራሽ አስተውሎት የታዳጊዎች የክረምት መርሀ ግብር ስልጠና ተጀመረ። የሰው ሰራሽ አስተውሎት የታዳጊዎች የክረምት መርሀ ግብር ስልጠና ችግር ፈቺ ምርምር በማድረግ በዘርፉ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ለማጎልበት የሚያስችል መሆኑን የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ገለጿል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሶስተኛው ዙር የታዳጊዎች የክረምት ስልጠና ማስጀመሪያ መርኃ ግብር በሳይንስ ሙዚየም ተከናውኗል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገትና የኢኮኖሚ ሽግግር አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የማይተካ ሚና እንዳለው በመግለጽ በዘርፉ ላይ መስራት እንደሚገባ በተለያዩ መድረኮች ማንሳታቸው ይታወሳል።   በተለይም ትውልዱ ላይ መልካም ዘር በመዝራት የወደፊቷን የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ማድረግ እንደሚገባም ማሳሰባቸው እንዲሁ። ኢትዮጵያ ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ ተነጥላ መቀመጥ እንደማትችልና በዘርፉ እየተከናወነ ያለው ስራ አበረታች መሆኑንም መጠቆማቸው አይዘነጋም። የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ ለሶስተኛው የታዳጊዎች የክረምት ስልጠና መርኃ ግብር ከሶስት ሺህ በላይ ታዳጊዎች ተመዝግበው 201 ተመርጠዋል።   በዓለም ላይ በፍጥነት እያደገ የመጣውን የሰው ሰራሽ አስተውሎት የሚመጥን የሰው ሀይል ለማፍራት በታዳጊዎች ላይ መስራት ይገባል ብለዋል። ለዚህም በሰው ሰራሽ አስተውሎት ምርምር በማድረግ የሀገራቸውን ችግር የሚፈቱና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን መስራት የሚችሉ ታዳጊዎችን እያሰለጠኑ መሆኑን ገልጸዋል። ኢንስቲትዩቱ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የክረምት ሰልጣኝ ታዳጊዎች ችግር ፈቺ ፕሮጀክቶችን እንዲያፈልቁ ለማስቻል አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል።
በሂግሎሌ ወረዳ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀመረ
Jul 19, 2024 394
ሂግሎሌ፤ ሐምሌ 12/2016(ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል ሂግሎሌ ወረዳ 600 ኪሎ ዋት የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ሚኒ-ግሪድ ፕሮጀክት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀመረ። ፕሮጀክቱን መርቀው ዛሬ አገልግሎት ያስጀመሩት የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኢነርጂ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ እና የሶማሌ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ናቸው። በሥነስርዓቱ ላይ የተገኙት የሶሚሌ ክልል መስኖና ተፋሰስ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መሐመድ ፈታ እንደገለጹት፤ በፕሮጀክቱ ከዋና የኤሌክትሪክ ማሰራጫ ጣቢያ በ180 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው የወረዳው ህዝብ የዓመታት የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ተመልሷል። በዚህም የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል።   አቶ መሐመድ እንዳሉት ፕሮጀክቱ 5ሺህ 600 አባውራዎችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ከፀሐይ ብርሃን የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲያገኙ ማድረጉ በቀጣይ የወረዳውን ህዝብ ሁለንተናዊ የብልፅግና ጉዞ ዕውን ለማድረግ ያግዛል። ሚኒ-ግሪድ ፕሮጀክቱ 75 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገበት ሲሆን ለቀጣይ 25 ዓመታት እንደሚያገለግልም ተመላክቷል። በፕሮጀክቱ ምረቃ ላይ የተሳተፉት የማህበረሰቡ መሪ ዑጋዝ ፋራህ ሳህል እና የአገር ሽማግሌዎች የዘመናት የህዝብ ጥያቄ በመመለሱ ደስታቸው ወሰን እንደሌለው ገልጸዋል።  
የተደራጀ መረጃን በፍጥነት የሚያደርሱ ዘመናዊ የሚቲዎሮሎጅ መረጃ መሰብሰቢያ አውታሮችን የማስፋት ስራ እየተከናወነ ነው- ኢንስቲትዩቱ
Jul 18, 2024 347
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 11/2016(ኢዜአ):- የተደራጀ መረጃን በፍጥነት የሚያደርሱ ዘመናዊ የሚቲዎሮሎጅ መረጃ መሰብሰቢያ የመሰረተ ልማት አውታሮች ዝርጋታ እያከናወነ መሆኑን የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለፀ። በተ.መ.ድ የልማት ፕሮግራም ድጋፍ በትግበራ ላይ በሚገኘው ''የቅድመ ማስጠንቀቂያዎች ለሁሉም'' ኢኒሼቲቭ ላይ ያተኮረ የባለድርሻ አካላት የሁለት ቀናት የውይይት መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። በኢኒሼቲቩ ከታቀፉ 13 የአፍሪካ ሀገራት መካከል አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ በመድረኩ ላይ የእስከዛሬ ተሞክሮዋን አቅርባለች። ውይይቱ በኢኒሼቲቩ ዕቅድ፣ ትግበራ እና ለቀጣይ ግብዓት በሚሆኑ አበይት ጉዳዮች ላይ መምከሩን የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጅ ኢንስቲቲዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ ለኢዜአ ተናግረዋል። በተለይም ዕውቀት መር መረጃ አሰባሰብ፣ የአየር ትንብያ ስርዓት ምልከታዎችን የማጠናከር እና በመረጃ ተደራሽነት ዙሪያ በዝርዝር መምከሩን ተናግረዋል። የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት ሊመጣ የሚችለውን አደጋ ወደ መልካም አጋጣሚ በመለወጥ ምርትና ምርታማነት እንዲሰፋ ዕድል እንደሚፈጥር ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። በውይይቱ የተነሱ ሃሳቦችን በማደራጀት የአደጋ ስጋትን የሚቀንሱ ፕሮጀክቶች እንደሚተገበሩ ገልጸው፤ ይህም ለተቋሙ አቅም ይፈጥራል ብለዋል። ኢንስቲትዩቱ በፍጥነት እና በተደራጀ መልኩ መረጃ የሚያደርሱ ዘመናዊ የሚቲዎሮሎጅ መረጃ መሰብሰቢያ የመሰረተ ልማት አውታሮችን የማስፋት ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ከባለድርሻ አካላት ጋር ያለውን ቅንጅታዊ አሰራር በማጎልበት የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓትን ይበልጥ እንደሚያጠናክርም ነው ዋና ዳይሬክተሩ ያረጋገጡት።                  
የፀሐይ ሃይል ፕሮጀክቶች የአርሶ አደሩ እና የአርብቶ አደሩ ልጆች ጥራት ያለው ትምህርትን እንዲያገኙ አስችሏል - የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር 
Jul 18, 2024 215
ጅግጅጋ፤ ሐምሌ 11/2016 (ኢዜአ)፦ በትምህርት ቤቶች አገልግሎት መስጠት የጀመሩት የፀሐይ ሃይል ፕሮጀክቶች የአርሶ አደሩ እና የአርብቶ አደሩ ልጆች ጥራት ያለው ዘመናዊ ትምህርትን እንዲያገኙ ማስቻሉን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ገለጸ። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከሶስት ሚሊዮን በላይ የገጠር ነዋሪዎች በአማራጭ ቴክኖሎጂ የፀሐይ ሐይል የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ መደረጋቸውም ተገልጿል። በውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) የተመራው የመንግስት ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች ቡድን በሶማሌ እና ሐረሪ ክልሎች በቴክኖሎጂ የታገዘ የፀሐይ ሃይል ፕሮጀክቶችን መርቀው ስራ በማስጀመር ላይ ናቸው። ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ (ዶ/ር) እንደገለፁት፤ ባለፉት ሁለት ቀናት በምስራቅ የአገሪቷ ክልሎች ተመርቀው ወደ ስራ የገቡት የፀሐይ ሐይል ፕሮጀክቶች ሚኒስቴሩ የገጠሩን ህብረተሰብ የኢነርጂ ፍላጎት ለማሟላት የጀመራቸው ተግባራት ማሳያዎች ናቸው። በተለይም በትምህርት ቤቶች አገልግሎት መስጠት የጀመሩት ፕሮጀክቶች የአርሶ አደሩን እና የአርብቶ አደሩን ልጆች ጥራት ያለው ዘመናዊ ትምህርትን አግኝተው ለአገር አለኝታ እንዲሆኑ ያስችላሉ ብለዋል። በመሆኑም በየደረጃው የሚገኙ የገጠር የአመራር አካላት፤ መምህራንና ህብረተሰቡ ፕሮጀክቶቹ ዘላቂ ጥቅም እንዲሰጡ አስፈላጊውን እንክብካቤ ማድረግ እንደሚገባቸው አሳስበዋል። በሚኒስቴሩ የኢነርጂ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ከዋና የኤሌክትሪክ ማሰራጫዎች ርቀው የሚገኙ የገጠር የህብረተሰብ ክፍሎችን የኢነርጂ ተጠቃሚ ለማድረግ አበረታች ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ።   በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ በቴክኖሎጂ የታገዙ ከ350 በላይ የሶላር አማራጭ የሃይል ምንጮችን በገጠራማ የአገሪቷ ክፍሎች በመትከል ከሶስት ሚሊዮን በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። በተለይም በ156 ትምህርት ቤቶች እና መለስተኛ የጤና ተቋማት የፀሐይ ሐይል ተጠቃሚ በመሆናቸው የገጠሩን ህብረተሰብ ሁለንተናዊ ህይወትና አኗኗር እየለወጠ መሆኑን አውስተዋል። የፀሐይ እና የውሃ ሃብትን በአነስተኛ ቴክኖሎጂ በመታገዝ የገጠሩን ህብረተሰብ ፍትሐዊ የኢነርጂ ተጠቃሚ ከማድረግ ጎን ለጎን ቴክኖሎጂው በአነስተኛ የመስኖ ስራዎች ላይ በመተግበር ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ይሰራል ብለዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለፃ የተገኙትን አበረታች ውጤቶች ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ ከተለያዩ አጋር አካላት እና ዩኒሴፍን ከመሳሰሉ ዓለም አቀፍ ተቋማት የተቀናጀ ስራ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። "በቀጣይም አማራጭ የሶላር ኃይልን በትላልቅ ተቋማት ተደራሽ የማድረጉ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል" ብለዋል። ከ600 እስከ 700 ኪሎ ዋት ኃይል ማመንጨት የሚችሉ የፀሐይ ኃይል ፕሮጀክቶችን በገጠራማ የአገሪቷ አካባቢዎች የማስፋፋት ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የገለፁት ደግሞ በሚኒስቴሩ የገጠር ኢነርጂ ቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር ስራ አስፈፃሚ አቶ ብርሃኑ ወልዱ ናቸው።   በገጠር የተጀመሩ ስራዎችን በማጠናከር በ2030እ.ኤ.አ አብዛኞዎቹ የገጠር የህብረተሰብ ክፍሎች የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን ዋና ዋና የማሰራጫ ተቋማት ግንባታም ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን በመጠቆም። ዛሬም በሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) የተመራው ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች ቡድን በሶማሌ ክልል የተለያዩ ዞንና ወረዳ የገጠር ቀበሌዎች ተገኝቶ ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ይመርቃሉ።  
ኢንስትቲዩቱ ግብርናን የሚያዘምኑ የዲጂታል የአሰራር ስርዓት ይፋ አደረገ
Jul 16, 2024 598
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 9/2016(ኢዜአ)፦ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስትቲዩት ግብርናን የሚያዘምኑ ሁለት የዲጂታል የአሰራር ስርዓት ይፋ አድርጓል። ይፋ የተደረጉት የግብርና አሰራርን የሚያዘምኑ 'አውቶሜሽን ኢንፑት ቮቸር' እና ('ኢ_ቮቸር 2.0') የተሰኙ ናቸው። በመርሀግብሩ የኢንስትቲዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬው ተገኝ (ዶ/ር)ን ጨምሮ የባለድርሻ አካላትና የተቋሙ አመራሮች ታድመዋል። ይፋ የተደረጉት አሰራሮች ዘላቂ ገበያ፣ የተሻለ ምርት እንዲሁም የተሻለ የግብርና ግብአቶች ስርጭት እንዲኖር ከማድረጉም ባለፈ የገበያ ትስስር ስርአት ወቅቱን የጠበቀና ትክክለኛ መረጃ የሚቀርብበት እንደሆነም ተገልጿል። በተጨማሪ አርሶ አደሮች የግብርና ምርቶችን ያለ ማንም ጣልቃ ገብነት ምርት ለሚገዙ እንዲያቀርቡ የሚያስችል ነው።   አሰራሩ የአርሶ አደሮችና የግብርና ምርት ሸማቾችን ትስስር ከማጠናከር ባለፈ የገበያ ዋጋ መረጃዎችን ማግኘት እንደሚያስችል ተገልጿል። የኢ-ቮውቸር 2.0 ስርአት ደግሞ ተሻሽሎ የቀረበ የዲጂታል አማራጭ ሲሆን የግብርና ግብአት የሆኑት ዘርና ማዳበሪያ የሚሰራጭበት ነው። ከዚህ ቀደም የግብአት አቅርቦት በወረቀት እንደነበር እና ይህንንም ወደ ዲጂታል የሚቀይር ስርዓት መሆኑ ተመላክቷል። የግብርና ምርምር ኢንስትቲዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬው ተገኝ ዶ/ር በዚሁ ወቅት እንዳሉት ከኢንስቲቲዩቱ አንዱ ተልዕኮው በግብርናው ዘርፍ ላይ ያሉ ማነቆዎች በመለየት መፍትሄ ማስቀመጥ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም ተለዋዋጭ በሆነው አለም ውስጥ የዘርፉን ተግዳሮቶች በመለየት መፍትሄዎችን እያመለከተ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ዛሬ ይፋ የተደረጉ የአሰራር ስርዓቶች የዚሁ አካል መሆናችውን ገልጸዋል። በቀጣይም በዘርፉ ያሉ ተግዳሮቶችን የመለየት እና የመፍትሄ አቅጣጫ የማመላከት ስራዎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥልተናግረዋል። ለፕሮጀክቱ እውን መሆን አስተዋጽኦ ላደረጉ አጋር ተቋማት ምስጋና አቅርበዋል።                  
በኢትዮጵያ የኤሌክትሮኒክስ ፓስፖርት ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የዲዛይን ስራ ተጠናቋል
Jul 12, 2024 1092
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2016(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የኤሌክትሮኒክስ ፓስፖርት ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል የዲጂታል ዲዛይን ስራ መጠናቀቁን የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አስታወቀ። የተቋሙ ሀላፊዎች የ2016 በጀት ዓመት አፈጻጸምና በ2017 በጀት አመት የሚከናወኑ ተግባራት ላይ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ዳይሬክተሯ ሰላማዊት ዳዊት በመግለጫቸውም ተቋሙ በ2016 በጀት ዓመት ያከናወናቸውን ዋና ዋና የለውጥ ተግባራትና እቅድ አፈጻጸም ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በዚህም በፓስፖርት አገልግሎት፣ አሰራርን ከማዘመንና ከተገልጋዮች የሚነሱ ቅሬታዎችን በመፍታት ረገድ እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን ገልጸዋል። ዋና ዳይሬክተሯ በመግለጫው በዚህ ዓመት አገር ውስጥ የነበረው የቡክሌት መጠን በማነሱ ከፍተኛ ውዝፍ እንደነበር አስታውሰው ችግሩን ለመፍታት 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን የፓስፖርት ቡክሌት ከውጭ በማስገባት 1 ነጥብ 1 ሚሊዮኑ ታትሞ ለተገልጋዮች ተደራሽ መደረጉን ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥ ከ101 ሺህ በላይ የሚሆነው ፓስፖርት በውጭ ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ተደራሽ መደረጉንም እንዲሁ፡፡ በየዕለቱ ፓስፖርት የማተም አቅምን ቀደም ሲል ከነበረው 2 ሺህ ወደ 14 ሺህ ማሳደግ መቻሉንም ነው የተናገሩት። ተቋሙ የሪፎርም ስራዎችን ተግባራዊ በማድረግ 14 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን ተናግረው፤ ይህም ከባለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጻር ሶስት እጥፍ እድገት ያሳየ መሆኑን አስረድተዋል። በአዲስ አበባ በየቀኑ በኦንላን አመልካቾችን የመቀበል አቅም ከ900 ወደ 1 ሺህ 700 ማደጉን ገልጸው፤ በአጠቃላይ በአገር አቀፍ ደረጃ በኦን ላይን ማመልከቻን የመቀበል አቅም በአማካኝ 90 በመቶ መድረሱን ገልጸዋል። የኤሌክትሮኒክስ ፓስፖርት ተደራሽ ለማድረግም የዲጂታል ፓስፖርት ዲዛይን ስራ መጠናቀቁን ጠቁመው፤ ይህም ሃሰተኛ ሰነድን ከመከላከል፣ ደንበኞች በተቀላጠፈ መንገድ እንዲስተናገዱ በማድረግ በአጠቃላይ ከፓስፖርት ጋር ተያይዞ የሚስተዋሉ ህገ-ወጥነትን ያስቀራል ብለዋል። ለፖስፓርት ህትመት የሚወጣውን የውጭ ምንዛሬ ለማስቀረት ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ በተመሳሳይ ለውጭ አገር ዜጎች የሚሰጠው የመኖሪያ መታወቂያና በውጭ ለሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን የሚሰጠው መታወቂያ ላይም በኤሌክትሮኒክስ የታገዘ እንዲሆን ለውጥ ይደረጋል ብለዋል።   የተቋሙ ምክትል ዋና ዳሬክተር ጎሳ ደምሴ በበኩላቸው የመዳረሻ ቪዛ በ188 አገራት ክፍት በተደረገው መሰረት ከ820 ሺህ በላይ የውጭ አገር ዜጎች የቪዛ አገልግሎት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ተቋሙ ከ51 ሺህ በላይ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ዲያስፖራዎች መታወቂያ መስጠቱን ጠቅሰው ከእነዚህ ውስጥ 65 በመቶ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድን (ዶ/ር) ጥሪ ተቀብለው የመጡ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ ለሚኖሩ ከ34 ሺህ በላይ የውጭ አገር ዜጎች ጊዜያዊና ቋሚ የመኖሪያ ፈቃድ የተሰጠ ሲሆን ህጋዊ የመኖሪያ ፈቃድ የሌላቸው ላይ የተወሰደውን የማስተካከያ እርምጃም ዘርዝረዋል። ሃሰተኛ የመኖሪያ ፈቃድ፣ በትውልደ ኢትዮጵያውያን መታወቂያ፣ ቪዛና ሌሎች ሃሰተኛ ሰነዶች ሲገለገሉ የነበሩ ከ18 ሺህ በላይ የውጭ አገር ዜጎች በቅጣት ከአገር እንዲወጡ መደረጉን አብራርተዋል። ተቋሙ ከ240 በላይ በህገ-ወጥ ተግባራት ላይ የተሳተፉ ሰራተኞችና ደላሎች ላይ ዕርምጃዎችን መውሰዱን ገልፀው፤ በቀጣይም ይህ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። ከሲቪል ምዝገባና ሌሎች የ2016 በጀት ዓመት የተከናወኑ ተግባራት በመግለጫው የተነሱ ሲሆን በ2017 አገልግሎትን ከማዘመን፣ ምቹ የስራ አካባቢን ከመፍጠር፣ ተደራሽነትን ከማስፋት፣ የተገልጋይ ዕርካታን ከማረጋገጥ አኳያ የተያዙ ዕቅዶች ላይ የተቋሙ ኃላፊዎች ማብራሪያ ሰጥተዋል።    
የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በማስፋት ዜጎች የሚያገኙትን አገልግሎት ቀልጣፋ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ነው 
Jul 11, 2024 1023
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2016(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በማስፋት ዜጎች የሚያገኙትን አገልግሎት ግልጽ፣ ቀልጣፋና ውጤታማ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ገለጸ። ሚኒስቴሩ ከአጋር ድርጅቶች ጋር በመተባበር የኢትዮጵያ መንግሥት ለቀጣይ አምስት ዓመታት የሚመራበትን የዲጂታል መንግሥት ስትራቴጂና የመንግሥት ኢንተርፕራይዝ አርክቴክቸር የጥናት ሠነድን በተመለከተ ውይይት አካሂዷል። በመድረኩ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ 21ኛውን ክፍለ ዘመን የሚመጥን ዲጂታል መሰረተ-ልማት ለመገንባት በትኩረት እየሰራች ነው ብለዋል። ለዚህም ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን በመቅረጽ የኢትዮጵያን የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ማሳለጥ የሚያስችሉ የለውጥ እርምጃዎች ተግባራዊ መደረጋቸውን ገልጸዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ልማት በዜጎች ተሳትፎ የመንግሥትን አገልግሎት ግልጽና ቀልጣፋ በማድረግ የመንግሥትን የመፈጸም አቅም እያጎለበተ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ስትራቴጂ መሰረት በማድረግ በቀጣይ አምስት ዓመታት ተግባራዊ የሚሆን የዲጂታል መንግሥት ስትራቴጂ መዘጋጀቱን ነው የገለጹት። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን አለማየሁ (ዶ/ር)፤ የዲጂታል መንግሥት ስትራቴጂና ኢንተርፕራይዝ ሰነድ ለአንድ ዓመት ያክል ሲዘጋጅ መቆየቱን ገልጸዋል።   መድረኩም አጋር አካላትን በመጋበዝ በስትራቴጂ ሰነዱ ላይ መካተት የሚገባቸውን ግብዓቶች በመጨመር ስትራቴጂው መጽደቅ የሚችልበትን ምዕራፍ ለማጠናቀቅ ያለመ ነው ብለዋል። ስትራቴጂ ሰነዱ የዜጎችን የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የመንግሥት አገልግሎት ፈጣንና ቀልጣፋ እንዲሁም ግልጸኝነት የተላበሰ በማድረግ አገልግሎት አሰጣጡን ለማጠናከር ያለመ መሆኑንም ነው ያስረዱት።   በኢትዮጵያ የአውሮፓ ኅብረት የትብብር ኃላፊ ሮቤርቶ ሺሊሮ፤ ኅብረቱ በዜጎች ኑሮ ላይ ተጨባጭ ለውጥ በሚያመጡ የኢኮኖሚ መስኮች ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር እየሰራ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ እየተከተለች ያለው የዲጂታል ሥርዓት ግንባታ የገበያውን ሥርዓት በማቅናትና በማሳለጥ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ አዎንታዊ አበርክቶ ይዞ እንደሚመጣ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። በመድረኩም ስትራቴጂ ሰነዱን በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ የመነሻ ጽሁፎች ቀርበው ምክክር ተደርጎባቸዋል።  
በስፔስ ሳይንስ ዘርፍ ተወዳዳሪ ለመሆን የሰው ኃይል የማብቃትና የመደገፉ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል -ሚኒስቴሩ 
Jul 10, 2024 1081
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2016(ኢዜአ)፦ በስፔስ ሳይንስ ዘርፍ ተወዳዳሪ ለመሆን የሰው ኃይል የማብቃትና የመደገፉ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። ስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢኒስቲትዩት ከቦይንግ እና ፋሴሳ ከተሰኙ ድርጅቶች ጋር በመተባበር በስፔስ ቴክኖሎጂ ዙሪያ ያሰለጠናቸውን ከ120 በላይ ተማሪዎች አስመርቋል። ተመራቂዎቹ በስልጠና ቆይታቸው አነስተኛ መጠን ያለው ሳተላይት (ኪውብሳት) ጽንጸሀብ፣ ሳተላይቶች ሲመጥቁ የሚቆዩበት ከባቢ ያለው ግፊት፣ መጠነ ሙቀት እና የጨረር ሁኔታን ተገንዝበው ለዚህ የሚስማማ ሳተላይት ግንባታ ላይ ግንዛቤ እንዲጨብጡ መደረጉ ተገልጿል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን ዓለማየሁ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ በዓለም አቀፍ ደረጃ በዲጂታል ዘርፍ ተወዳዳሪ ለመሆን በስፔስ ዘርፉ ግንዛቤያቸው የላቁ ወጣቶችና ታዳጊዎችን ማፍራት ይገባል። በሰው ሰራሽ አስተውሎት እንዲሁም በስፔስ ሳይንስ ዙሪያ ወጣቶች አዳዲስ እውቀቶችን መገብየት አለባቸው ያሉት ሚኒስትር ደኤታው መሰል ስልጠናዎች ፋይዳቸው የጎላ ነው ብለዋል። በስፔስ ሳይንስ ዘርፍ የሰው ኃይል ለማብቃት መንግሥት በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን ጠቁመው በቀጣይም መሰል ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። ቦይንግ ኩባንያን ጨምሮ በመስኩ ላይ ከሚሰሩ ድርጅቶችና ተቋማት ጋርም መንግሥት በትብብር እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።   የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ በበኩላቸው በስፔስ ሳይንስ ዘርፍ ባለሙያዎችን ለማፍራት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር በትብብር እየተሰራ ነው። ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ጋር በመቀናጀት በአስትሮኖሚ፣ ስፔስ ሳይንስ፣ ሪሞት ሴንሲንግን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች በሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪ ባለሙያዎችን ለማፍራት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በሦስተኛ ዲግሪ ከ20 በላይ እንዲሁም በሁለተኛ ዲግሪ ከ35 በላይ ባለሙያዎች ተመርቀው ወደ ሥራ ዓለም መቀላቀላቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል። በተመሳሳይም ኢኒስቲትዩቱ ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ ጋር በመተባበር በኤሮኔቲክ እንጂነሪንግና በኤሮስፔስ ኢንጂነሪንግ በድህረ ምረቃ ባለሙያዎችን እያፈራ መሆኑን ተናግረዋል። በስፔስ ዘርፍ ተሰጥኦ እና ፍላጎት ያላቸውን ታዳጊዎች ክህሎት ለማሳደግ ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ የልጆች ስፔስ ክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከል መቋቋሙን ገልጸው በማዕከሉ በርካታ ተማሪዎች ግንዛቤና እውቀታቸውን እንዲያሳድጉ እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። በዚህም ለአገሪቷ ተስፋ ሰጪ የሆኑ ፕሮጀክቶችን መንደፍና የሙከራ ምርት ማምረት የቻሉ ተማሪዎችን መፍጠር ተችሏል ነው ያሉት።   የቦይንግ ኩባንያ የአፍሪካ ዳይሬክተር አምባሳደር ሄኖክ ተፈራ እንዳሉት፤ ቦይንግ በኢትዮጵያም ሆነ በአፍሪካ ስፔስ ኢንዱስትሪውን ለማሳደግ ራይዕ ሰንቆ እየተንቀሳቀሰ ነው ብለዋል። ቦይንግ ኩባንያ ወጣቱ ትውልድ በስፔስ ኢንዱስትሪው የጎላ አስተዋጽኦ እንዲያበረክት የሚያደርግውን ድጋፍ እንደሚያጠናክር አረጋግጠዋል።   ከተመራቂዎች መካከል ተማሪ ቃልኪዳን ስጦታው በስፔስ ኢንዱስትሪው ለኢትዮጵያ የምችለውን ለማድረግ ዝግጁ ነኝ ብላለች። ሌላው ተመራቂ ደግማዊ ዳዊት በበኩሉ ስልጠናው በእውቀትና ክህሎት አቅማችንን የበለጠ እንድናጎለብት ዕድል ፈጥሮልናል ብሏል።      
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም