ሳይንስና ቴክኖሎጂ
''ክህሎት ኢትዮጵያ'' ፕሮግራም በዓለም አቀፍ ደረጃ  አሸናፊ እንድንሆን አስችሎናል-የክህሎት ውድድር አሸናፊዎች 
Aug 26, 2025 171
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2017 (ኢዜአ)፦ ''ክህሎት ኢትዮጵያ'' ፕሮግራም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተሸላሚ ለመሆን እንዳስቻላቸው በቻይና በተካሄደው የክህሎት ውድድር ያሸነፉ ተሳታፊዎች ገለፁ። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በቻይና በተካሄደው የክህሎት ውድድር አሸናፊ ለሆኑት ወጣቶች ትናንት በቢሯቸው አቀባበል አድርገውላቸዋል።   ከብሪክስ አባል ሀገራት የተውጣጡ ከ300 በላይ ወጣቶች በተሳተፉበት የቻይና የክህሎት ውድድር ኢትዮጵያዊያን የወርቅ፣ የብርና የነሐስ ሜዳሊያ አሸናፊ ሆነዋል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የውድድሩ አሸናፊዎች እንደ ሀገር የተጀመረው ''ክህሎት ኢትዮጵያ'' ፕሮግራም በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንድንሆን አስችሎናል ብለዋል። በውድድሩ የወርቅ ሜዳሊያ አሸናፊ የሆነው ወጣት ዘላለም እንዳለው በመድረኩ ባቀረበው የዲጂታል ግብርና አካል የሆነ ስማርት የመስኖ መቆጣጠሪያና መከታተያ የፈጠራ ሥራ የወርቅ ሜዳሊያ ተሸልሟል።   ያቀረበው የፈጠራ ሃሳብ በግብርና ዘርፍ የሚያጋጥመውን ተግዳሮት በዲጂታል መንገድ በመታገዝ ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑን ተናግሯል። ሁለተኛ የወጣው ወጣት አቤኔዘር ተከስተ በበኩሉ በፈጠራ ባዳበረው በማንዋል የሚሰራ የፕላስቲክ ቅርጽ ማውጫ የብር ሜዳሊያ ተሸላሚ መሆኑን ተናግሯል።   የሰራው ማሽን በአነስተኛ ዋጋ ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ የፕላስቲክ ቁሳቁሶችን ማምረት እንደሚችል አስታውቋል፡፡ የአንድን ሀገር ብልፅግና ለማረጋገጥ የክህሎት ልማት ወሳኝ መሆኑን የተናገረው አቤኔዘር የጀመረውን የክህሎት ልማት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጿል። ወጣት ነቢሀ ነስሩ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ላይ የተመሰረተና በሆስፒታሎች ታማሚዎች ነርስ ለመጥራት የሚያስችላቸውን የጥሪ “Nurse calling System” የፈጠራ ሀሳብ ለውድድር አቅርባ ሶስተኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳሊያ መሸለሟን ተናግራለች።   የፈጠራ ሃሳቡ በታካሚዎች እና በነርሶች መካከል ያለውን የተግባቦት ሂደት ዲጂታላይዝ በማድረግ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል መሆኑን ገልፃለች። በክህሎት ኢትዮጵያ ያገኘችው ስልጠና በውድድሩ ውጤታማ እንድትሆን እንዳስቻላትም ጠቅሳለች።
ኢትዮ-ቴሌኮም የዜጎችን ተጠቃሚነት መሰረት ያደረገ የሶስት ዓመት ሰው ተኮር አዲስ አድማስ ስትራቴጂ ይፋ አደረገ
Aug 26, 2025 137
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮ-ቴሌኮም የዜጎችን ተጠቃሚነት መሰረት ያደረገ የሶስት ዓመት ሰው ተኮር አዲስ አድማስ ስትራቴጂ ይፋ አደረገ። ተቋሙ ከ2018 እስከ 2020 ዓ.ም የሚተገበር የሶስት ዓመት የቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ እና የ2018 በጀት ዓመት ዕቅዱን ይፋ አድርጓል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ አዲስ አድማስ የቀጣይ ሶስት ዓመት ስትራቴጂ አዲስ ጅማሮ አዲስ ተስፋ እና አዲስ ዕይታን የያዘ ነው።   ስትራቴጂው ብሔራዊ ስትራቴጂና ዕቅዶችን፣ ዓለም አቀፍ ሁነቶችን እንዲሁም የፋይናንስ አካታችነትን ታሳቢ አድርጎ የተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል። አዲስ አድማስ ስትራቴጂ ሰው ተኮር ራዕይ የያዘ በየዘርፉ የተያዙ ዕቅዶች እንዲሳኩ የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። ስትራቴጂው ትብብርና አንድነት፣ ልህቀት፣ ዕምነትና ጥምረት፣ ፈጠራና ማህበራዊ ሀላፊነትን ለማሳካት ያለመ አዲስ እይታ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የዲጂታል ሽግግር ለማጠናከር ለዲጂታል ቴክኖሎጂ ቅድሚያ መስጠት እና የደንበኞችን ፍላጎት መሰረት ማድረግ የቀጣይ ትኩረቶች መሆኑንም ጠቅሰዋል። አዳዲስ እውቀትና ክህሎት የሚጠይቁ ቴክኖሎጂዎች የሚመጥን የሰው ሀይል ማፍራት፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ፈጣን አገልግሎት መስጠት፣ የሚተማመኑበት ተቋም መገንባት የስትራቴጂው ትኩረት መሆኑን ገልጸዋል። የደንበኞችን እርካታ ማላቅ፣ ኦፕሬሽናል ልህቀትን ማሳደግ፣ የሰራተኞችን ብቃት መለካት እና የገበያ መሪነቱን ማረጋገጥ የስትራቴጂው ስኬታማነት መለኪያዎች መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
በቻይና በተካሄደው የክህሎት ውድድር የተመዘገበው ውጤት በክህሎት ዘርፍ የማንሰራራት ብስራት ነው -ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Aug 26, 2025 114
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2017(ኢዜአ)፦ በቻይና በተካሄደው የክህሎት ውድድር የተመዘገበው ውጤት ሀገራዊ የክህሎት ዘርፍ የማንሰራራት ድል ብስራት ነው ሲሉ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። የውድድሩ አሸናፊዎች ኢትዮጵያ በክህሎት ልማት እያከናወነች ያለውን አመርቂ ተግባር ለዓለም ያረጋገጡበት እንደሆነም ገልጸዋል።   የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በቻይና በተካሄደው የክህሎት ውድድር አሸናፊ ለሆኑት ወጣቶች ትናንት በቢሯቸው አቀባበል አድርገውላቸዋል። ከብሪክስ አባል ሀገራት የተውጣጡ ከ300 በላይ ወጣቶች በተሳተፉበት የቻይና የክህሎት ውድድር ኢትዮጵያዊያን የወርቅ፣ የብርና የነሐስ ሜዳሊያ አሸናፊ ሆነዋል። ለ11ኛ ዙር በቻይና ጎዋንዡ በተካሄደው ውድድር ኢትዮጵያን የወከሉትና በተለያዩ ዘርፎች የፈጠራ ሀሳባቸውን ያቀረቡት ዘላለም እንዳለው አንደኛ፤ አቤኔዘር ተከስተ ሁለተኛ እንዲሁም ነቢሀ ነስሩ ሶስተኛ በመውጣት ነው ሜዳሊያቸውን ያገኙት። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በዚሁ ወቅት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ከለውጡ ወዲህ መንግስት በሪፎርም ከለያቸው አጀንዳዎች አንዱ የክህሎት ልማት ነው። ለክህሎት ልማት የተሰጠው ልዩ ትኩረት ፍሬ እያፈራ መምጣቱን የገለጹት ሚኒስትሯ፤ በስልጠና ብቻ ሳይሆን በቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ ውጤት እየታየ መሆኑን ተናግረዋል። በተሰሩት አበረታች ተግባራት በዓለም አደባባይ ሀገርን ማስጠራት የሚያስችል ውጤት እየተመዘገበ መምጣቱን በአብነት አነስተዋል። የወጣቶች እምቅ አቅም ላይ መስራት ከተቻለ ለሀገርም ሆነ ለዓለም ችግር የበለጠ መፍትሄ የሚሰጡ የፈጠራ ሃሳቦችን ማፍለቅ እንደሚቻል ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በማንሰራራት ሂደት ውስጥ እንዳለች ያነሱት ሚኒስትሯ፤ በውድድሩ የተመዘገበው ውጤት የክህሎት ዘርፍ የማንሰራራት ድል ብስራት ነው ሲሉ ገልፀዋል። በቻይና የተካሄደው የክህሎት ውድድር ኢትዮጵያ ያላትን እምቅ አቅም ያሳየችበት መሆኑን ጠቅሰዋል።
በቻይና የተካሄደው የክህሎት ውድድር ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን እምቅ አቅም ያሳየችበት ነው - የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Aug 25, 2025 199
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2017(ኢዜአ)፡- በቻይና የተካሄደው የክህሎት ውድድር ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን እምቅ አቅም ያሳየችበት መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። ኢትዮጵያን በመወከል በውድድሩ ያሸነፉት ተወዳዳሪዎች ሀገራችን በክህሎት ልማት ላይ እየሰራች እንዳለ በዓለም የክህሎት አደባባይ ያረጋገጡበት እንደሆነም ገልጸዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በቻይና በተካሄደ የክህሎት ውድድር አሸናፊ የሆኑትን ወጣቶች በቢሯቸው አቀባበል አድርገውላቸዋል። ከብሪክስ አባል ሀገራት ከተውጣጡ ከ300 በላይ የተሳተፉበት የቻይና የክህሎት ውድድር ኢትዮጵያዊያን የወርቅ፣ የብርና የነሐስ ሜዳሊያ አሸናፊ ሆነዋል። ለ11ኛ ዙር በቻይና ጎዋንዡ በተካሄደው ውድድር ላይ ኢትዮጵያን ወክለው ከተወዳደሩት ወጣቶች መካከል ዘላለም እንዳለው 1ኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ፣ አቤኔዘር ተከስተ 2ኛ በመውጣት የብር ሜዳሊያ አሸናፊ ሲሆን፤ ነቢሀ ነስሩ 3ኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳሊያ አግኝተዋል።   የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በዚሁ ወቅት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ከለውጡ ወዲህ መንግስት በክህሎት ልማት ላይ በትኩረት እየሰራ ነው። በዚህ አበረታች ውጤት እየተመዘገበ እንዳለ አንስተው፤ በዓለም አደባባይ በመወዳደር ሀገርን ማስጠራት እየተቻለ ነው ብለዋል። በቻይና የተካሄደው የክህሎት ውድድር ኢትዮጵያ ያላትን እምቅ አቅም ያሳየችበት መሆኑን ተናግረዋል። ሌሎች ወጣቶች ክህሎታቸውን በማውጣት እና ተቋማት በጋራ መስራት ከቻሉ የበለጠ ውጤት እንደሚያመጡ ገልጸዋል።  
የውሃ እና ተያያዠ የናሙና ምርመራ ማድረግ የሚያስችል ስፔሻላይዝድ ላብራቶሪ በቅርቡ ወደ ስራ ይገባል
Aug 24, 2025 221
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 18/2017(ኢዜአ)፡-ስድስት አይነት የውሃ እና ተያያዠ ናሙና ምርመራ ማድረግ የሚያስችል ስፔሻላይዝድ ላብራቶሪ በቅርቡ ስራ እንደሚጀምር የኢትዮጵያ ውሃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢትየጵያ ውሃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ስፔሻላይዝድ ላብራቶሪ መሪ ስራ አስፈጻሚ አብዱራሀማን ሰይድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢንስቲትዩቱ ከተለያዩ ተቋማት በሚቀርቡለት የውሃ ናሙናዎች ላይ ምርመራ አድርጎ ውጤቱን ይፋ ያደርጋል፡፡ ኢንስቲትዩት በማይክሮ ባይሎጂካልና በፊዚኮ ኬሚካል ዘርፍ የምርመራ አገልግሎቶችን እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። በፊዚኮ ኬሚካል ላቦራቶሪ በውሃ ውስጥ ያሉ ኬሚካሎችን መጠን በመለካት ውሃው ለሚፈለገው አገልግሎት መዋል የሚችል መሆኑን የማረጋገጥ ምርመራ እየሰጠ እንደሚገኝ ገልፀዋል። እንዲሁም በማይክሮባዮሎጂ ላቦራቶሪ በውሃ ውስጥ ያሉ በሽታ አምጪ ተዋህስያንን መለየትና መተንተን የሚያስችል ምርመራ እንደሚያከናውን ነው ያስረዱት። ኢንስቲትዩቱ ዘመናዊ ስፔሻላይዝድ ላብራቶሪ ግንባታ እያካሄደ መሆኑን ጠቅሰው፤ ግንባታው ሲጠናቀቅ ስድስት አይነት የውሃ ምርመራ አገልግሎቶችን መስጠት የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል። ኢንስቲትዩቱ በቀጣይ የአካባቢና የህዝብን ጤና ለመጠበቅ የሚያስችሉ ቶክሲኮሎጂ የውሃ ምርመራ እንዲሁም ለውሃ ሀብት አስተዳደር ጠቃሚ መረጃ የሚሰጠውን የአኳቲክ ባዮሎጂ ምርመራ የሚሰጥ እንደሚሆን ተናግረዋል። እንዲሁም የአፈርና የድንጋይ ፊዚካል እና ሜካኒካል ባህሪዎችን በማጥናት በመጠጥ ውሃ ላይ የሚያሳድሩትን ተፅእኖ ለመረዳት የሚያስችል ጂኦቴክኒካል ምርመራ በቅርቡ መስጠት የሚጀመር መሆኑን አስታውቀዋል። የተጀመሩ ስራዎች በዋነኝነት ኢትዮጵያ ለውሃ ምርመራ የምታወጣውን የውጭ ምንዛሬ ለማስቀረት ትልቅ ሚና እንደሚኖረው ነው የገለፁት።
በአማራ ክልል በዕውቀትና ክህሎት የታነፀ ትውልድ ለመገንባት ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል -ርዕሰ መስተዳደር አረጋ ከበደ
Aug 23, 2025 200
ባሕርዳር፤ ነሐሴ 17/2017 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በዕውቀትና ክህሎት የታነፀ ትውልድ ለመገንባት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አረጋ ከበደ ገለጹ። ‎በቀጣይ አምስት ዓመታት ከ5 ሚሊዮን በላይ ወጣቶችን ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል የዲጂታል ኢኒሼቲቭ ማስጀመሪያ መርሐ ግብር ዛሬ በባሕር ዳር ከተማ ተካሂዷል።   ‎የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በማጠቃለያው ላይ እንደገለጹት፤ ቴክኖሎጂን መፍጠር፣ መጠቀምና መተግበር የሚችል ትውልድ ለማመቻቸት ትኩረት ተሰጥቷል። ‎ለዚህም በክልል ደረጃ ዛሬ ተግባራዊ ማድረግ የተጀመረው የዲጂታል አማራ ኢኒሺቲቭ በቴክኖሎጂ ፈጠራ፣ ዕውቀትና ክህሎት የላቁ ዜጎችን ለማፍራት ታልሞ እንደሆነ ተናግረዋል። ‎ክልሉ ባዘጋጀው የ25 ዓመት አሻጋሪ የልማትና ዕድገት ዕቅድ ላይም በዲጅታል ቴክኖሎጂ የልማት ግቦችን ለማሳካት መመላከቱንም አንስተዋል። ‎ከ2018 እስከ 2022 ዓ.ም በሚተገበረው የዲጂታል አማራ ኢኒሸቲቭ ከ5 ሚሊየን በላይ ወጣቶችን በማሰልጠን ተጠቃሚ ለማድረግ ግብ መያዙን አስታውቀዋል። የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት በየደረጃው እያለው አመራር ራሱን ከወዲሁ አዘጋጅቶ መትጋት እንደሚጠበቅበት ጠቅሰው፤ በዘርፉ የተሰማሩ መምህራንም ለዲጂታል ኢኒሼቲቭ ውጤታማነት ራሳቸውን አስተዋጽኦ ማድረግ እንዳለባቸውም አመልክተዋል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ወቅቱን የዋጁ፣ የተረዱ፣ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ዕውቀትና ክህሎት ያላቸው ዜጎች ለማፍራት የዲጂታል አማራ ኢኒሸቲቭ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም በዲጂታል ቴክኖሎጂ የተደገፈ ትምህርት በማስታጠቅ ልጆቹ በፍጥነት መረጃ አግኝተው የመማር ማስተማር ስራው ሳቢ እና ከዘመኑ ጋር አብረው የሚራመዱ እንዲሆኑ ያግዛል ብለዋል። የዜጎች የዲጂታል ዕውቀታቸው ጎልብቶ ክህሎታቸውን በማሳደግ ዓለም አቀፍ የኦን ላይን ቢዝነስ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለሚደረገው ጥረት ስኬታማነት ሁሉንም ባለድርሻ አካላት መደገፍ እንዳለባቸው ገልጸዋል። ለዚህም ክልሉ በአሁኑ ወቅት ዘርፈ ብዙ የዲጂታል ኢኒሺቲቮችን ስራ ላይ ለማዋልና ከሰው ንክኪ ነፃ የሆኑ አገልግሎቶችን ተግባራዊ ለማድረግ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ቴክኖሎጂ እየዘመነና እየተስፋፋ መምጣቱን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ አቤል ፈለቀ ናቸው።   የትምህርት ተደራሽነትን በጥራትም ለማረጋገጥ የኢንተርኔት አገልግሎት ማስፋፋት፤ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን ማቅረብና የዲጂታል መሰረተ ልማት ግንባታዎችን ቅድሚያ ሰጥቶ ማሟላት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። አካል ጉዳተኞችን ጨምሮ ለሁሉም ተማሪዎች ተደራሽና ከባሕል ጋር ተዛማጅነት ያለው ዲጂታል ይዘት ያለው ቴክኖሎጂ ማዘጋጀት እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡ በመድረኩ ላይ የክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋንቱ ተስፋዬን ጨምሮ ሌሎችም ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተሳትፈዋል።      
በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መሰረታዊ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎት እያገኘን ነው - የስልጠናው ተሳታፊዎች
Aug 23, 2025 172
ጅማ፤ ነሐሴ 17/2017(ኢዜአ)፡- በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መሰረታዊ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎት እያጎለበቱ መሆኑን በጅማ ከተማ ስልጠናውን እየተከታተሉ የሚገኙ የመንግስት ሰራተኞች እና ተማሪዎች ተናገሩ። በጅማ ከተማ ስልጠናውን እየተከታተሉ የሚገኙ የመንግሰት ሰራተኞች እና ተማሪዎች ከስልጠናው ዘርፈ ብዙ ጥቅም እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ እየሰለጠነ የሚገኘው ምትኩ አብደታ ስልጠናው በዘመናዊ ዲጂታል ቴክኖሎጂ ዙሪያ ተጨባጭ እውቀት መጨበጥ እንዳስቻለው ተናግሯል። በተመቻቸላቸው የአትዮ ኮደርስ ስልጠናም አራቱንም ኦንላይን ስልጠናዎች መውሰዳቸውን ጠቅሶ በተለይም የዳታ ሳይንስና የኤ.አይ (AI) ኮርሶች ትልቅ አቅም እንደፈጠሩለት ገልጿል። ሌላው የመንግስት ሰራተኛ አብዱሰላም ጠይብ፤ በክረምቱ ወራት ስልጠናውን ተከታትሎ መጨረሱ ክህሎቱን እንዳዳበረለት ይገልጻል። ስልጠናው ለተለያዩ የሙያ አይነቶች የሚያግዝ በመሆኑ ስልጠናውን ያልወሰዱ የመንግስት ሰራተኞች ቢወስዱ ትልቅ ጥቅም ያገኛሉ ብሏል። በወሰደው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዙሪያ የተሻለ እውቀት ማግኘቱን የገለጸው ደግሞ ተማሪ አባስ አለሙ ሲሆን ወደ ፊት በዚህ ዘርፍ የራሱን የስራ እድል ለመፍጠር ማቅዱን ተናግሯል። በስልጠና ቆይታው ያገኘውን እውቀት እና ክህሎት ተጠቅሞ በሞባይል መተግበርያ ዙሪያ ስራዎችን ለመስራት እንደሚጥር ነው የተናገረው። ስልጠናው በትምህርት፣ በስራ እድል ፈጠራና ክህሎት እንዲሁም በሲቪል ሰርቪስ ጽህፈት ቤቶች አስተባባሪነት እየተሰጠ መሆኑም ተገልጿል። ስልጠናውን ከሚያስተባብሩ ጽህፈት ቤቶች አንዱ የሆነው የጅማ ከተማ አስተዳደር ሲቪል ሰርቪስ ጽህፈት ቤት የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ የስራ ሂደት መሪ ናስር አማን፤ ስልጠናው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎትን በማሳደግ የሰራተኛውን የመፈጸም አቅም ለማጎልበት ይረዳል ብለዋል። ጽህፈት ቤቱ በከተማ አስተዳደሩ ስር ያሉ የመንግስት ሰራተኞች፣ ተማሪዎችና መምህራን ስልጠናውን እንዲወስዱ አስፈላጊ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸው ስልጠናው ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል።
ከ5 ሚሊዮን በላይ ወጣቶች በዲጂታል ዕውቀትና ክህሎት ላይ ያተኮረ የኦንላይን ቢዝነስ ስልጠና እንዲያገኙ ይደረጋል - የአማራ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ
Aug 23, 2025 162
ባሕርዳር፤ ነሐሴ 17/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ከአምስት ሚሊዮን የሚበልጡ ወጣቶችን በዲጂታል ኢኒሼቲቭ የኦንላይን ቢዝነስ ስልጠና ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚሰራ የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ አስታወቀ። ‎"በዲጂታል ዕውቀትና ክህሎት የታነፀ ትውልድ ለአሻጋሪና ዘላቂ ዕድገት" በሚል መሪ ሃሳብ የዲጂታል ኢንሼቲቭ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በባሕርዳር ከተማ እየተካሄደ ነው።   ‎በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። ‎በማስጀመሪያ መድረኩ ላይ የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ አቤል ፈለቀ እንደገለጹት፤ እስከ 2022 ዓ.ም ከ5 ሚሊዮን በላይ የክልሉን ወጣቶች በዲጂታል ዕውቀትና ክህሎት ላይ ያተኮረ የኦንላይን ቢዝነስ ስልጠና እንዲያገኙ ይደረጋል። ‎ለዚህም የማመቻቸት ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው፤ በሂደቱም በትምህርት ላይ ለውጥ ለማምጣትና የኦን ላይን የስራ ዕድል ፈጠራን ተደራሽ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። ‎የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን የማስፋፋት፣ የፈጠራ ሃሳብና ችግር ፈቺ ትውልድን ለመገንባት እየተሰራ እንደሚገኝም አንስተዋል።   ‎በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ‎የዲጂታሉ ዓለም በፈጠነ የዕድገት ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ዘመኑን የዋጀ ትውልድ ለመገንባት መምህራን ራሳቸውን ሊያዘጋጁ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ለዚህም የሚያግዙ ከ9ኛ እስከ 12ኛ ክፍል ተማሪ ተኮር የማስተማሪያ ሞጅሎች እየተዘጋጁ እንደሚገኙም ጠቅሰዋል። ‎ስልጠናው የኦን ላይን ቢዝነስ ላይ አተኩሮ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ አተኩሮ እንደሚሰጥ ተመልክቷል።
"ለመንገዴ" የሞባይል መተግበሪያ የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት የሚያገኙ ዜጎችን ክብርና ደህንነት መጠበቅ ያስችላል
Aug 21, 2025 218
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15/2017(ኢዜአ)፦ "ለመንገዴ" የሞባይል መተግበሪያ የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት የሚያገኙ ዜጎችን ክብርና ደህንነት መጠበቅ የሚያስችል መረጃ የሚሰጥ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ገለጸ፡፡ በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና በዓለም አቀፍ ሥራ ድርጅት ትብብር የበለጸገው ''ለመንገዴ'' የሞባይል መተግበሪያ ይፉ ሆኗል።   የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ነቢሃ መሐመድ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት የሚያገኙ ዜጎችን ክብርና ደህንነት ማስጠበቅ የሚያስችሉ አሰራሮች ገቢራዊ እየተደረጉ ነው፡፡ በኢትዮጵያውያን የበለጸገው "ለመንገዴ" የሞባይል መተግበሪያ የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪትን በማዘመን ዜጎች ከቅድመ ጉዞ ዝግጅት ጀምሮ በመዳረሻ ሀገራት እንግልት እንዳይገጥማቸው ጠቃሚ መረጃ የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የሥራ ስምሪት የሚወስዱ ዜጎችን መብትና ግዴታ፣ የአሰሪና ሰራተኛን የሥራ ግንኙነት እንዲሁም ከውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት ሲመለሱ በሀገራቸው የራሳቸውን ሥራ መጀመር እንዲችሉ ግንዛቤ ያስጨብጣል ብለዋል፡፡ የክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የማሰልጠኛ ተቋማትን፣ ምርመራ የሚሰጥባቸው የጤና ማዕከላትን፣ የሥራ ስምሪት መዳራሻ ሀገራትን የኢትዮጵያ ኤምባሲና ቆንስል ቢሮዎች አድራሻ የሚያሳይ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በዚህም ዜጎች በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት ወቅት ችግር ቢገጥማቸው ለሚመለከተው አካል ጥቆማ መስጠት ያስችላቸዋል፤ የዜጎችን መብትና ደህንነት ለማስጠበቅ የሚደረገው ጥረትም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ የዓለም ሥራ ድርጅት የኢትዮጵያ፣ ጅቡቲ፣ ሶማሊያ፣ ሱዳን እና ደቡብ ሱዳን ዳይሬክተር ኩምቡላ ንዳባ በበኩላቸው፤ የውጭ ሀገር ስራ ስምሪት ለሚያገኙ ኢትዮጵያውያን ጥበቃና ደህንነት ወሳኝ መሆኑ አንስተዋል፡፡ "ለመንገዴ" የሞባይል መተግበሪያ የኢትዮጵያና የዓለም ሥራ ድርጅትን የጋራ ጥረት የሚያንጸባርቅ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ፣ በዓለም አቀፍ ድርጅቶች እና በማህበራዊ አጋሮች መካከል ያለው ትብብር አጉልቶ የሚያሳይ መሆኑንም ተናግረዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ የሥራ ስምሪት ለዜጎች ደህንነት ወሳኝ መሆኑን በመግለጽ፤ ኢትዮጵያ መሰል የቴክኖሎጂ ስራዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል የምታደርገውን ጥረት እንደግፋለን ብለዋል፡፡ "ለመንገዴ"ን አገልግሎት በቴሌ ብር መተግበሪያ ላይ ማግኘት እንደሚቻል ተገልጿል።
በውጭ ሀገር በሚፈጠሩ የስራ ዕድሎች ዜጎች መብትና ደህንነታቸው ተጠብቆ የሚሰሩበት የቴክኖሎጂ አቅም እየተፈጠረ ነው - የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር
Aug 21, 2025 288
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15/2017(ኢዜአ)፦ በውጭ ሀገራት በሚፈጠሩ የስራ ዕድሎች ዜጎች መብትና ደህንነታቸው ተጠብቆ የሚሰሩበት የቴክኖሎጂ አቅም እየተፈጠረ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር አስታወቀ። በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና በዓለም አቀፍ ሥራ ድርጅት ትብብር የበለጸገው ''ለመንገዴ'' የተሰኘ የሞባይል መተግበሪያ ይፉ ሆኗል። በዚሁ ጊዜ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ነቢሃ መሐመድ፤ የውጭ ሀገራት የሥራ ዕድል ስምሪት ሥርዓትን የሚያዘምኑ የማሻሻያ እርምጃዎች እየተወሰዱ ይገኛል ብለዋል። በተለይም በቴክኖሎጂ ዘርፍ የተወሰዱ የለውጥ እርምጃዎች ዜጎች በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት መብትና ደኅንነታቸው ተጠብቆ ተጠቃሚ የሚሆኑበት ሥርዓት መፈጠሩን ገልጸዋል። በራስ አቅም የበለጸገው የኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መር ሥርዓትም የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት አገልግሎትን በማዘመን ዜጎች በመዳረሻ ሀገራት የሚያጋጥማቸውን እንግልት መቅረፍ እንዳስቻለ አስታውቀዋል። በዛሬው ዕለት ይፋ የተደረገው ''ለመንገዴ'' የሞባይል መተግበሪያም ዜጎች የሥራ ስምሪት ከመውሰዳቸው በፊት የቅድመ ጉዞ ዝግጅት የሚያደርጉበትን ጠቃሚ መረጃ እንደሚሰጥ ተናግረዋል። የሥራ ስምሪት የሚወስዱ ዜጎችም መብትና ግዴታ እንዲሁም የአሰሪና ሠራተኛን የሥራ ግንኙነት ግንዛቤ የሚያስጨብጥ መሆኑን አብራርተዋል። በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት የወሰዱ ዜጎችም ወደ ኢትዮጵያ ሲመለሱ ማህበረሰባቸውን በመቀላቀል የራሳቸውን ሥራ መጀመር የሚችሉበት ጠቃሚ መረጃ የሚሰጥ መሆኑንም አስገንዝበዋል። የክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የማሰልጠኛ ተቋማትና ምርመራ የሚሰጥባቸው የጤና ተቋማትንና የሥራ ስምሪት መዳረሻ ሀገራትን የኢትዮጵያ ኤምባሲና ቆንስል ቢሮዎች አድራሻ ያሳያል ብለዋል። የሞባይል መተግበሪያው ዜጎች በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት ችግር ቢገጥማቸው ለሚመለከተው ኣካል ጥቆማ መስጠት በሚችሉበት አግባብ መበልጸጉንም አስረድተዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ዜጎች መብትና ደህንነታቸው ተጠብቆ በውጭ ሀገር ከሚፈጠሩ ሥራ ዕድሎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማስቻል የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
የጂንካ ዩኒቨርሲቲ የእንስሳት ምርታማነትን በማሳደግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማጎልበት እየሰራ ነው
Aug 21, 2025 129
ጂንካ፤ነሐሴ 15/2017 (ኢዜአ):- የእንስሳት ጤና አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግና የእንስሳት ምርታማነትን በማሳደግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማጎልበት እየሰራ መሆኑን የጂንካ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ። ዩኒቨርሲቲው በአሪ እና በደቡብ ኦሞ ዞኖች አርሶና አርብቶ አደር አካባቢዎች የተሻሻለ የእንስሳት ጤና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ፕሮጀክት ይፋ አድርጓል። በደቡብ ኦሞ እና በአሪ ዞን በተካሄደው የፕሮጀክት ማስጀመሪያ ፕሮግራም የዩኒቨርሲቲው ምክትል ፕሬዚዳንት መልካሙ ዘሮ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ አካባቢው በርካታ የእንስሳት ሀብት ያለበት በመሆኑ የእንስሳቱን ጤና በመጠበቅና ዝርያ በማሻሻል ምርቱን በእጥፍ ለማሳደግ እየተሰራ ይገኛል። ዛሬ በዩኒቨርሲቲው ይፋ የተደረገው ፕሮጀክትም የእንስሳት ጤና አገልግሎት ተደራሽ ባልሆነባቸው ገጠራማ አካባቢዎች አገልግሎቱን በቅርበት ተደራሽ በማድረግ ማህበረሰቡን ለማገዝ ያስችላል ብለዋል። የዩኒቨርስቲው የእንስሳት ጤና ሳይንስ የትምህርት ክፍል ተመራማሪ እና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ዱባለ በየነ (ዶ/ር) ፕሮጀክቱ ሁለት ዋና አላማዎችን ይዞ የተቋቋመ መሆኑን ጠቅሰው የአርሶና የአርብቶ አደሩን የኑሮ ዘይቤ ያማከለ የተሻሻለ የእንስሳት ጤና አገልግሎት መስጠት ዋነኛ አላማው እንደሆነም ጠቁመዋል። እንዲሁም በእንስሳት ህክምና ተመርቀው ስራ ያላገኙ ወጣቶችን በማደራጀትና የህክምና ቡድን በማቋቋም በጤና ባለሙያዎች እጥረት ምክንያት አገልግሎቱ ተደራሽ ባልሆነባቸው አካባቢዎች ለመገኘት ፕሮጀክቱ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። ለፕሮጀክቱ ትግበራ ዩኒቨርስቲው ለጤና ባለሙያዎች ስልጠና በመስጠት፣ መድኃኒቶችን እና የህክምና ቁሳቁሶችን በማሟላት እገዛ እያደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። በባካዳውላ አሪ ወረዳ ሴኔጋል ቀበሌ በተካሄደው የፕሮጀክት ማስጀመሪያ መረሃ ግብር ላይ የተገኙት የአሪ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ጉራልቅ ይዥማልቅ፥ አካባቢው የተሻሻለ የእንስሳት ዝርያ በስፋት የሚገኝበትና በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የወተት ክላስተር እንዲሆኑ ከተመረጡ አካባቢዎች አንዱ መሆኑን ገልጸዋል። የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ዛሬ ይፋ ያደረገው ፕሮጀክትም የእንስሳቱን ጤና በማሻሻል ምርታማነትን ለመጨመር አጋዥ እንደሆነም ተናግረዋል ። በደቡብ ኦሞ ዞን እና በአሪ ዞን እየተተገበረ ባለው ፕሮጀክት ተጠቃሚ ከሆኑ የእንስሳት ጤና ባለሙያዎች መካከል ወጣት አብነት ሶይተየር እና ገነት ገረሙ ይገኙበታል። ወጣቶቹ ዩኒቨርስቲው ይፋ ባደረገው ፕሮጀክት የስራ ዕድል ማግኘታቸውን ጠቅሰው በሰለጠኑበት የሙያ መስክም በቅርበት ማህበረሰባቸውን ለማገልገል ዕድል በማግኘታቸው መደሰታቸውንም ገልፀዋል።    
የውሃ ስማርት ቴክኖሎጂዎችን ለገጠር ማህበረሰብ በሰፊው ተደራሽ ይደረጋል - ኢንስቲትዩቱ
Aug 21, 2025 150
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15/2017(ኢዜአ)፡- በቀላሉ ጥቅም ላይ የሚውሉ የውሃ ስማርት ቴክኖሎጂዎችን ለገጠሩ ማህበረሰብ በሰፊው ተደራሽ ለማድረግ ዝግጅት መጠናቀቁን የኢትዮጵያ ውሃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ፡፡ የኢንስቲትዩቱ ቴክኒካል ድጋፍ መሪ ስራ አስፈጻሚ አይችሉህም ዘነበ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢንስቲትዩቱ የውሃ አቅርቦትን የሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎች እንዲተላለፉ እያደረገ ይገኛል፡፡ በበጀት ዓመቱ በቀላሉ ጥቅም ላይ የሚውሉ የውሃ ስማርት ቴክኖሎጂዎችን ለገጠሩ ማህበረሰብ በሰፊው ማሰራጨት የሚያስችል ዝግጅት እየተጠናቀቀ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ ቴክኖሎጂዎቹን ከከተማ በራቁና የውሃ ተጠቃሚ ባልሆኑ አካባቢዎች በሰፊው ለማሰራጨት 21 ሳይቶች መለየታቸውን ጠቁመው፤ አካባቢዎቹ ከአምስት እስከ አስር ሜትር ባለ ርቀት ከመሬት ውስጥ በቀላሉ ውሃ የሚገኝባቸው መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የቴክኖሎጂዎቹ ውጤታማነት ፍተሻ ተካሂዶባቸው ጥራታቸው መረጋገጡን ስራ አስፈጻሚው ጨምረው አስታውቀዋል፡፡ ቴክኖሎጂዎቹ ለመጠጥ፣ ለምግብ ማብሰያ፣ ለመታጠቢያ እንዲሁም ለእንስሳትና ለጓሮ አትክልት የሚሆን ውሃ ለመሳብ ያላቸው ጠቀሜታ የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። በሌላ በኩል ኢንስቲትዩቱ በውሃ ቴክኖሎጂ ዘርፍ ከሰላሳ አንድ በላይ በሚሆኑ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ለሚማሩ 2ሺህ 500 በላይ ሰልጣኞች የቴክኒክ ድጋፍ ማድረጉን አንስተዋል። ኢንስትቲዩቱ በኤሌክትሮኒክ ሜካኒካል፣ በድሪሊንግ፣ በወተር ሰፕላይ፣ በኢሪጌሽን ድሬኒንግ ቴክኖሎጂ ምዘና እየሰጠ መሆኑንም አስታውቀዋል፡ ተቋሙ ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ ከ2 ሺህ 500 በላይ ለሆኑ የውሃ ባለሙያዎች የብቃት ማረጋገጫ ምዘና መስጠቱን አመልክተዋል፡፡
የአፍሪካ  ሀገራት ኢ-ተገማች በሆነችው ዓለም አይበገሬነት መገንባት እና የኢኖሼሽን መፍትሄዎችን መተግበር ይኖርባቸዋል - ህብረቱ
Aug 21, 2025 170
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2017(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሀገራት ለተለዋዋጭ እና ኢ-ተገማች ዓለም የሚሆን ጠንካራ አቅም መገንባት እና የኢኖሼሽን መፍትሄዎችን መተግበር እንደሚገባቸው የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። ዘጠነኛው የጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም (ቲካድ) ዛሬ በዮካሃማ መካሄድ ጀምሯል። በፎረሙ ላይ የጃፓን ጠቅላይ ሚኒስትር ሺገሩ ኢሺባ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር እና የአንጎላ ፕሬዝዳንት ጆአኦ ሎሬንቾና የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች ተገኝተዋል። “የአፍሪካ እና ጃፓን የጋራ መፍትሄዎችን መፍጠር” የፎረሙ መሪ ሀሳብ ነው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በፎረሙ ላይ ባደረጉት ንግግር አፍሪካና ጃፓን ለሶስት አስርት ዓመታት የዘለቀ ወዳጅነት እንዳላቸው ገልጸዋል። ሁለቱ ወገኖች ዘላቂና መዋቅራዊ የልማት ለውጥ ለማምጣት የሚያስችል የፈጠራ መፍትሄዎችን በጋራ መቅረጽ እንደሚገባቸው አመልክተዋል። ኢኖቬሽን የሀገራቱ ትብብር የማጠናከር አካል ማድረግ እንደሚያስፈልግ የገለጹት ሊቀ መንበሩ ዘርፉ አካታችነትን ለማረጋገጥ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል። ሊቀ መንበሩ አህጉራዊ ማዕቀፎችን አንስቶ ባነሱት ሀሳብ ላይ የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና (AfCFTA) ለንግድ፣ ኢንዱስትሪ እና ለፈጠራ ስራ እድገት አንቀሳቃሽ ሞተር መሆኑን ነው የገለጹት። አጀንዳ 2063 ከቲካድ እና ከዘላቂ ልማት ግቦች ጋር የተቆራኘ መሆኑን ተናግረዋል።   ፎረሙን በጋራ ያዘጋጀው የዓለም ባንክ የአፍሪካ የረጀም ጊዜ ራዕይ ለማሳካት የሚያስችል የፋይናንስ ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል። ከጂኦ ፖለቲካ አኳያም በዓለም ላይ ያለው አለመራረጋጋት በአፍሪካ የልማት አጅንዳዎች ላይ አሉታዊ ተጽእኖዎች እያሳደረ ነው ብለዋል ሊቀ መንበሩ። የፋይናንስ አቅርቦት መቀነስ፣ የታሪፍ ጫናዎች ፣ ኢ-ተጋማችነት እና ተለዋዋጭ ሁኔታዎች የአፍሪካን ለውጥ እያስተጓጎሉ መሆኑን ገልጸዋል። የአፍሪካ ሀገራት ያሉ ፈተናዎችን የሚቋቋም አቅም መፍጠር እና የኢኖሼሽን መፍትሄዎችን መተግበር እንዳለባቸው ነው የተናገሩት። አፍሪካ እና ጃፓን ዘላቂ፣ ለውጥ አምጪና ሁሉን አካታች እድገት የሚያመጡ የኢኖሼሽን ውጤቶች ለመጠቀም በጋራ እንደሚሰሩ ተናግረዋል። የአፍሪካ መጻኢ ጊዜ በአይበገሬነት፣ በፈጠራ እና ኢኖቬሽንን መሰረት ያደረገ ዓለም አቀፍ አጋርነት የሚወሰን መሆኑን ሊቀ መንበሩ አስገንዝበዋል። ዘጠነኛው የጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም (ቲካድ) አስከ ነሐሴ 16 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል። እ.አ.አ በ1993 የተጀመረው የጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም (ቲካድ) አፍሪካ እና ጃፓን በልማት፣ ሰላም እና ደህንነት ያላችውን ትብብር በባለብዙ ወገን ትብብርና አጋርነት ማጠናከር አላማ ያደረገ ነው።
የኢትዮጵያን የፀሐይ ኃይል ልማት ለመደገፍ በቁርጠኝነት እንሰራለን - የዓለም አቀፍ የፀሐይ ኃይል ጥምረት
Aug 20, 2025 191
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ያለውን ከፍተኛ የፀሐይ ኃይል ልማት ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን የዓለም አቀፍ የፀሐይ ኃይል ጥምረት (አይ.ኤስ.ኤ.) አስታወቀ። የዓለም አቀፍ የፀሐይ ኃይል ጥምረት ዋና ዳይሬክተር አሺሽ ከሀና ለኢዜአ እንደገለጹት÷ ኢትዮጵያ በፀሐይ ኃይል አማራጭ ከፍተኛ የመልማት ጸጋ ያላት ሀገር ናት። ለዚህ ይረዳ ዘንድ በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት የኢትዮጵያን የፀሐይ ኃይል ልማት ለማገዝ በሚያስችል የፕሮጀክትና የፖሊሲ ትብብር ላይ በጋራ ለመስራት የማዕቀፍ ስምምነት መደረጉን ገልጸዋል።   በዚህም በኢትዮጵያ 400 ሜጋ ዋት የፀሐይ ኃይል ማመንጨት የሚያስችል ፕሮጀክት ለመገንባት የተጀመረውን ጥረት ለማገዝ ቁርጠኛ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የፀሐይ ኃይል መሰረተ ልማት መስፋፋት የግል ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው አብራርተዋል። በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ቅጥር ግቢም 100 ሜጋ ዋት የሚያመነጭ የመኪና ማቆሚያ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ጣሪያ ፕሮጀክት በመገንባት ለአገልግሎት መብቃቱን ገልጸዋል። በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ቅጥር ግቢ ለአገልግሎት የበቃው የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት በቀጣይ ለሚተገበረው በፀሐይ ኃይል የሚሰራ የውሃ መሳቢያ ፕሮጀክት ትልቅ መሰረት እንደሚሆን አስገንዝበዋል። በተጨማሪም የዓለም አቀፍ የፀሐይ ኃይል ጥምረት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፀሐይ ኃይል ቴክኖሎጂ የልህቀት ማዕከል ኢትዮጵያዊያን ሙያተኞችን እያሰለጠነ እንደሚገኝ አንስተዋል። ኢትዮጵያ የወሰደችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በግሉ ዘርፍ የሚመራ ዕድገትና ኢንቨስትመንትን ማፋጠን የሚያስችል መሆኑንም አብራርተዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በፀሐይ ኃይል ልማት ዘርፍ የግሉን ዘርፍ የኢንቨስትመንት ፍሰት ለማሳደግ ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት የማይበገር የኢኮኖሚ ሥርዓት ለመገንባት ከምትሰራባቸው ዘርፎች መካከል የፀሐይ ኃይል ልማት ግንባር ቀደም ድርሻ ከሚሰጣቸው አንዱ መሆኑ ይታወቃል።  
በበጀት ዓመቱ በ15 ከተሞች የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ ይሆናል -ኢንስቲትዩቱ
Aug 20, 2025 244
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 14/2017(ኢዜአ)፦ በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት በ15 የኢትዮጵያ ከተሞች የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ሙሉ ለሙሉ እንደሚተገበር የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት አስታወቀ። በ10 ዓመት መሪ ልማት እቅዱ 73 ከተሞችን ከዲጂታል አድራሻ ስርዓት ጋር የማስተሳሰር እቅድ መያዙን ገልጿል። በኢትዮጵያ በየከተሞች ያለውን እድገትና መስፋፋት ተከትሎ ከቦታ ወደ ቦታ ለመንቀሳቀስ በቂ አድራሻ ማግኘት አስቸጋሪ ነው። ሌላው ቀርቶ ችግር ተፈጥሮ ለእርዳታ የሚንቀሳቀሱ የእሳት አደጋ መኪናና ተጎጂዎችን የሚያነሱ አምቦላንሶች ከተጠሩበት ቦታ የሚደርሱት ከብዙ ምሪት በኋላ እንደሆነ ለመታዘብ ይቻላል። ኢትዮጵያ ችግሩን ለመቅረፍ የዲጂታል አድራሻ ስርዓትን ከሐምሌ ወር 2014 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ እያደረገች ይገኛል። የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ማንኛውም ሰው በቀላሉ አንድን ቦታ ሊረዳው በሚችል መልኩ ለሰዎች ማሳወቅ የሚችልበት መገኛ ተኮር (location) አሰራር ነው። የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ አቶ አግማሴ ገበየሁ በዲጂታል ስርዓቱ አማካኝነት የቢሾፍቱ ከተማ የሙከራ ትግበራ ተጠናቆ በየካቲት ወር 2016 ዓ.ም አገልግሎቱ ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ መሆን መጀመሩን ለኢዜአ ገልጸዋል። የቢሾፍቱን መልካም ተሞክሮ በመውሰድ ስርዓቱን ወደ ሌሎች ከተሞች የማስፋፋት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በአዲስ አበባ፣ አዳማ፣ ሐረር፣ ባህር ዳር፣ ደብረ ብርሃን እና ጅማ ከተሞች የአየር ፎቶግራፍ የማንሳት፣ ዳታ ዝግጅት፣ አድራሻ መስጠት፣ የመረጃ ዝግጅት፣ የካርታ ዝግጅቶች እና ከዲጂታል ስርዓት የማስተሳሰርን ጨምሮ የተለያዩ ስራዎች በመገባደድ ላይ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። የስድስቱ ከተሞች የሙከራ ጊዜ ተጠናቆ እስከ ታህሳስ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ባለው ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ወደ ሙሉ ትግበራ እንደሚገባ ጠቁመዋል። በ2017 ዓ.ም በጀት ዓመት ስራቸው የተጀመረው ኮምቦልቻ፣ ጎንደር፣ አርባ ምንጭ፣ ሚዛን አማን፣ ወላይታ ሶዶ ፣ አዋሽ ሰባት፣ ሃዋሳ፣ ጅግጅጋ እና ድሬዳዋ ከተሞች የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ዝርጋታ በተያዘው በጀት ዓመት እንደሚጠናቀቅ ነው አቶ አግማሴ የገለጹት። በአጠቃላይ በተያዘው በጀት አመት በ15 ከተሞች ስርዓቱ ሙሉ ለሙሉ እንደሚተገበር ተናግረዋል። በተጨማሪም ኢንስቲትዩቱ ከከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ጋር በመሆን በዘንድሮው በጀት የ18 ከተሞች የዲጂታል ስርዓት ዝርጋታ ዝግጅት ስራዎች ለማጠናቀቅ እቅድ መያዙን አመልክተዋል። አድዋ፣ አምቦ፣ አዲግራት፣ ሽሬ፣ አክሱም፣ መቀሌ፣ ወልዲያ፣ ወልቂጤ፣ ባቱ፣ ቦንጋ፣ ፍቼ፣ ጋምቤላ፣ ጅንካ፣ ከሚሴ፣ ሮቤ፣ ሸገር፣ ወራቤ እና ወሊሶ የዝግጅት ስራ የሚከናወንባቸው ከተሞች ናቸው። እንደ አቶ አግማሴ ገለጻ፤ የ18ቱ ከተሞች ስራ በ2019 ዓ.ም በጀት ዓመት እንደሚጠናቀቅ ጠቁመዋል። የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ትግበራ እና ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወትም ነው የገለጹት። ዲጂታል አድራሻ ስርዓት አቅጣጫ ከመጠቆም ባለፈ እቃ ማድረስ (ዲሊቨሪ)፣ አምቡላንስ፣ የኤሌክትሮኒክ ግብይት (e-commerce)፣ መንገዶች፣ መሠረተ ልማቶች እና ሌሎች አገልግሎቶችን በኦን ላይን ተደራሽ ማድረግን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እንዳለውም አብራርተዋል። በ10 ዓመቱ መሪ ልማት እቅድ 73 ከተሞችን የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ተጠቃሚ ለማድረግ እቅድ ተይዞ እየተሰራ መሆኑን ስራ አስኪያጁ ጠቁመዋል።
ዩኒቨርሲቲው የ"ሞሪንጋ" ተክል ምርት ላይ እሴት በመጨመር የውጭ ምንዛሪ የሚያስገኝ ፕሮጀክት ቀርፆ ወደ ተግባር ገብቷል
Aug 19, 2025 161
አርባምንጭ፤ነሐሴ 13/2017 (ኢዜአ)፡-አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የ" ሞሪንጋ" ተክል ምርት ላይ እሴት በመጨመር የውጭ ምንዛሪ ማስገኘት የሚያስችል ፕሮጀክት ቀርፆ ወደ ተግባር መግባቱን አስታወቀ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጋሞና ወላይታ ዞኖች በ90 ሄክታር መሬት ላይ የሞሪንጋ ችግኝ ተከላ ለማከናወን ስራ ዛሬ ተጀምሯል። በመረሃ ግብሩ ላይ የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት አብደላ ከማል(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደናገሩት፥ በጋሞ እና ወላይታ ዞኖች በሚገኙ ሦስት ወረዳዎች የሞሪንጋ ምርትን እሴት በመጨመር የውጭ ምንዛሪ ማግኘት የሚያስችል ፕሮጀክት ተቀርጾ ወደ ተግባር ተገብቷል። ለዚህም ከተለያዩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ድርጅቶች ጋር በትብብር እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሰፊ የሞሪንጋ አቅም መኖሩን ጠቅሰው፥ዩኒቨርሲቲው ይህን አቅም በምርምር በማበልጸግ እሴት ተጨምሮበት ለሀገር ውስጥና ለውጪ ገበያ እንዲቀርብ እያመቻቸ መሆኑን ገልጸዋል። የሞሪንጋ ፕሮጀክቱ እሴት በመጨመር የሕብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ከማሳደግ ባሻገር ለአረንጓዴ አሻራ ራዕይ ስኬት ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለውም ጠቁመዋል። የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ተክሉ ወጋየሁ በበኩላቸው፤ በሞሪንጋ ፕሮጀክቱ የችግኝ ተከላ መረሃ ግብር በጋሞ ዞን ምዕራብ አባያ ወረዳ ፤በወላይታ ዞን ደግሞ አባላ አባያና ኪንዶ ኮይሻ ወረዳዎች ውስጥ በ90 ሄክታር መሬት ላይ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። ለአንድ ዓመት የሚቆየው ፕሮጀክቱ የሞሪንጋ ተክል ልማት ሂደት ከ20 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል። ፕሮጀክቱ ተግባራዊ በሆኑባቸው አከባቢዎች የማቀነባበሪያ ፋብሪካ እንደሚገነባና በዘርፉ የተሠማሩ በርካታ ማህበራት ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አስረድተዋል። ዩኒቨርሲቲው ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ ድጋፍ መገኘቱን የገለጹት ደግሞ የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አዲሱ ፈቃዱ(ዶ/ር) ናቸው። በጋሞ እና ወላይታ ዞኖች የተጀመረው የሞሪንጋ ፕሮጀክት ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ጠቁመዋል። የሞሪንጋ ምርቱ እሴት ተጨምሮበት የተለያዩ መድሃኒቶች፣ መዋቢያና የምግብ ዘይት በማምረት ከውጭ የሚገባውን ከመተካት ባለፈ የውጭ ምንዛሪ ግኝትን ለማሳደግ ያለው ፋይዳ ትልቅ መሆኑን ገልጸዋል።
ኢንስቲትዩቱ በውኃ ቴክኖሎጂ እና በብቁ የሰው ኃይል ግንባታ ሀገራዊና ቀጣናዊ አቅም እየፈጠረ ነው
Aug 17, 2025 203
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 11/2017(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ የውኃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት በውኃ ቴክኖሎጂ እና በብቁ የሰው ኃይል ግንባታ ሀገራዊና ቀጣናዊ አቅም ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ታመነ ኃይሉ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ኢንስቲትዩቱ ከአስራ አምስት በላይ ለሆኑ የአፍሪካ ሀገራት በውኃ ቴክኖሎጂ ዘርፍ ውጤታማ ስልጠና እየሰጠ እንደሚገኝ አስታውቋል። በዚህም የስልጠና ልህቀት ማዕከል መሆን የሚያስችለውን የአቅም ግንባታ እና ሎጂስቲክስ የማሟላት ስራ እያከናወነ መሆኑንም ገልጿል፡፡ የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ታመነ ኃይሉ(ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ኢንስቲትዩቱ በሀገሪቱ የውኃ ተደራሽነትን ለማሳደግ እየተሰሩ በሚገኙ ስራዎች የበኩሉን አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል፡፡ አርሶ አደሩን ጨምሮ ዜጎች በአነስተኛ ወጪ ውኃን ከከርሰ ምድር እንዲያገኙ ለማስቻል ቀላልና ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢንስቲትዩቱ አገልግሎቱን በማስፋት ዘርፉ የሚፈልገውን ድጋፍ ለማፋጠን እየሰራ መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል፡፡ በመላ ሀገሪቱ ለሚገኙ የውኃ ቴክኖሎጂ ባለሙያዎች በየጊዜው ተግባራዊ ስልጠናዎችን በመስጠት አቅም እየገነባ እንደሚገኝም አክለዋል፡፡ ሰልጣኞች በየክልላቸው የተለያዩ ጥገናዎችን በራስ አቅም በማካሄድ ለውኃ ተደራሽነት የበኩላቸውን እየተወጡ መሆናቸውንም ጠቁመዋል፡፡ ኢንስቲትዩቱ በውኃ ቴክኖሎጂ ዘርፍ ከሀገር አልፎ ቀጣናዊ አቅምን ለመገንባት እየሰራ መሆኑንም ነው ዋና ዳይሬክተሩ ጨምረው የተናገሩት፡፡ በዚህም ከአስራ አምስት በላይ ለሆኑ የአፍሪካ ሀገራት ባለሙያዎች ስልጠና እየሰጠ መሆኑን አንስተው በዚህም እስካሁን ከተለያዩ ሀገራት ለመጡ 218 ባለሙያዎች በተለይ በከርሰ ምድር የውኃ ቁፋሮ ዙሪያ ልዩ ስልጠና መስጠቱን ገልጸዋል፡፡ በቀጣናው የውሃ ቴክኖሎጂ ምርምርና የስልጠና ልህቀት ማዕከል ለመሆን ሎጂስቲክስ የማሟላት ስራ እያከናወነ እንደሚገኝም አንስተዋል።   በኢንስቲትዩቱ ስልጠና እየወሰዱ ያገኘናቸው ፍቅረ ዮሐንስ አሰፋ እና አሰድ ሙሃመድ ስልጠናው በተግባር የተደገፈ በመሆኑ በቂ እውቀት እያገኙበት እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡   በቀጣይ በስልጠናው ያገኙትን ሙያዊ ክህሎት በመጠቀም በአካባቢያቸው የውኃ ተደራሽነትን ለማሳደግ እንደሚሰሩ ገልጸዋል፡፡
እሴት የተጨመረበት ዲጂታል የፖስታ ሳጥን አገልግሎት በቅርቡ ሥራ ይጀምራል
Aug 16, 2025 311
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2017(ኢዜአ)፦ዘመኑን የዋጀ የፖስታ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል እሴት የተጨመረበት የዲጂታል ፖስታ ሳጥን በቅርቡ ሥራ እንደሚጀምር የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዳግማዊ ኃይልዬ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ፖስታ ከ130 ዓመታት በላይ በተሻገረ የረጅም ዘመን ታሪኩ እንደ አንጋፋነቱ ማደር ተስኖት ማትረፍ ቀርቶ እዳውን ለመክፈል ሲቸገር ቆይቷል፡፡ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ባደረገው ሁሉን አቀፍ ሪፎርም በ2016 ዓ.ም ኢትዮጵያ ተቋማት የስኬት ሽልማት ከተበረከተላቸው አምስት ተቋማት መካከል አንዱ መሆን ችሏል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በወቅቱ በእዳ የተዘፈቀ እና በመዘግየት የሚታወቀው የኢትዮጵያ ፖስታ ስር ነቀል ለውጥ በማድረግ ከአፍሪካ አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ስም ካላቸው ተስፋ ሰጭ ተቋማት መሰለፍ መቻሉን መግለጻቸው ይታወሳል፡፡ የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዳግማዊ ኃይልዬ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ተቋሙ በቴክኖሎጂና አሰራር ችግር ውስጥ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ ፖስታ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እና ለሀገር ኢኮኖሚ ማበርከት የሚገባውን አስተዋጽኦ መወጣት ባለመቻሉ በተደረገ ጥቅል ሪፎርም በፈጣን እድገት ምህዋር ውስጥ መግባቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ዓለም አቀፉ የፖስታ ሕብረት እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2023 ከሰሀራ በታች ያሉ የአፍሪካ ሀገራት ቀዳሚ ተብሎ ሽልማት ተበርክቶለታል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ፖስታ ከጥንት ጀምሮ ከሚታወቅባቸው አገልግሎቶች መካከል የፖስታ ሳጥን አንዱ መሆኑን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ አገልግሎቱን እሴት በመጨመር በዲጂታል ስርዓት ጥቅም ላይ እንዲውል ይደረጋል ብለዋል፡፡ ስለሆነም ደንበኞች ዘመናዊና የተሟላ የዲጂታል ፖስታ ሳጥን (vertual post box) አገልግሎት ማግኘት የሚችሉበት አሰራር እየተዘረጋ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የዲጂታል ፖስታ ሳጥን ደንበኞች አድራሻቸውን ሲቀይሩ በፍጥነት የሚያሳውቅ፤ ተቋሙም ያሉበትን ቦታ በትክክል አውቆ መልዕክቱን በፍጥነት ማድረስ የሚችልበት አሰራር መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ደንበኞች የተላከላቸውን መልዕክት በስልካቸው የሚከታተሉበት እንዲሁም አድራሻቸውን /KYC/ በሚቀይሩበት ወቅት ባሉበት ቦታ የሚያደርስ ዘመናዊና ፈጣን አገልግሎት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ የዲጂታል ፖስታ ሳጥን ለደንበኞች ተጨማሪ ክፍያ የማይጠየቅባቸው ሌሎች ጥቅል አገልግሎቶችን መያዙን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ ሰዎች በእለት ከእለት ኑሯቸው የሚጠቀሟቸው አገልግሎቶች መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ አገልግሎቱ የመጨረሻ የጥራት ማረጋገጫ ፍተሻ ላይ መድረሱን በመጥቀስ፤ እስከ መስከረም 2018 ዓ.ም መጨረሻ ይፋ ይደረጋል ብለዋል፡፡
በመዲናዋ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች ወደ ዲጂታል የክፍያ ሥርዓት ሊገቡ ነው
Aug 16, 2025 317
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2017(ኢዜአ)፦በመዲናዋ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች ከ2018 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ዲጂታል የትራንስፖርት አገልግሎት ክፍያ ሥርዓት እንደሚገቡ የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ገለጸ። አዲስ አበባ ከወረቀት የተላቀቀ አገልግሎትን ለመገንባት የስማርት ሲቲ ጉዞ ላይ ናት፤ በዚህ ረገድ የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ዘርፉን ለማዘመን የሚያስችሉ የተለያዩ ዲጂታል አሰራሮችን ጀምሯል፡፡ የቢሮው የኦፕሬሽን ዘርፍ ምክትል ኃላፊ ዳኛቸው ሽፈራው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የመዲናዋን የትራንስፖርት አገልግሎት ማዘመን የሚያስችሉ የአሰራር ማሻሻያዎች ተግባራዊ እየተደረጉ ነው፡፡   ቢሮው የትራንስፖርት ስርዓቱን በቴክኖሎጂ የማዘመን ስራ በቬሎሲቲና በከተማ አውቶብሶች መጀመሩን ጠቅሰው፤ ተቋማቱ በተለያዩ የዲጂታል አማራጮች አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ገልጸዋል። ከ2018 ዓ.ም ጀምሮ የብዙኃን ትራንስፖርት የሚሰጡ የከተማ አውቶብሶችን ጨምሮ በመዲናዋ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ አብዛኛው ተሽከርካሪዎች ወደ ዲጂታል የትራንስፖርት አገልግሎት ክፍያ እንደሚገቡ አስታውቀዋል፡፡ በስማርት ካርድ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚጠቀሙ የመዲናዋ ነዋሪዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ስማርት ካርድ መጠቀማቸው ጊዜያቸውን በአግባቡ ለመጠቀም ከማስቻሉ በላይ ከእንግልት መዳናቸውን አንስተዋል፡፡   ካነጋገርናቸው ተጠቃሚዎች መካከል ሲሳይ ብርሃኑ፤ እንዳለችው ስማርት ካርድ መጠቀሟ በየዕለቱ ትኬት ለመቁረጥ የምታደርገውን እንግልት ቀንሶላታል።   መታፈሪያ ኃይሉና ትዕግስት ይጥና በበኩላቸው፤ ስማርት ካርድ መጠቀማቸው ያለሰልፍ በቅድሚያ እንዲስተናገዱና ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል።   አመለወርቅ ሞሴ በበኩሏ አገልግሎቱ ከዚህ በፊት የነበረውን የሰልፍ መጨናነቅ ያስቀረና በወር አንድ ጊዜ ካርድ በመሙላት ወጪዋን በአግባቡ እንድታስተዳድር እየጠቀማት መሆኑን አንስታለች፡፡   የቬሎሲቲ ባስ ካፒቴኖች በበኩላቸው፤ የስማርት ካርድ ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ ቀልጣፋ የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት ማስቻሉን ጠቁመዋል፡፡   የባስ ካፒቴን ሮማን አሰፋ እንዳለችው፤ አገልግሎቱ ለተጠቃሚውና ለእነሱ ጊዜን በመቆጠብ የምልልስ መጠንን እንዲጨምሩ እያደረገ ነው፡፡   የባስ ካፒቴን ዳኜ ካሳ በበኩሉ፤ አገልግሎቱ ለተጠቃሚዎች እና ለአሽከርካሪዎች ከሚሰጠው ጥቅም ባሻገር ለስራቸው ቅልጥፍና ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግሯል፡፡
የኦሮሚያ ክልል ከተሞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ ታግዘው አገልግሎትና ልማታቸውን እንዲያፋጥኑ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Aug 15, 2025 193
አዳማ፤ ነሐሴ 9/2017(ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ከተሞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ ታግዘው አገልግሎትና ልማታቸውን እንዲያፋጥኑ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ መንግሥት ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አብዱልአዚዝ ዳውድ (ዶ/ር) ገለጹ። የስማርት አዳማ ግቦች ውጤታማነት፣ ቀጣይ የከተማዋ የልማትና ዕድገት ጉዞ ሂደት ላይ ያተኮረ መፅሐፍ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ተመርቋል።   በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የተገኙት የአሮሚያ ክልል መንግሥት ፕሬዚዳንት ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አብዱልአዚዝ ዳውድ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ የተሰናዳው መፅሐፍ የክልሉን ከተሞች አራት የልማት ግቦችና ቀጣይነት አቅጣጫ የቃኘ ነው። ይህም ከተሞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት ማስፋፋት፣ የክህሎት መር የስራ ዕድል ፈጠራን ለዜጎች ተደራሽ ማድረግና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንደማጣቀሻ የሚያገለግል መሆኑንም ጠቅሰዋል። በቀጣይ በክልሉ ከተሞች ሁለንተናዊ ልማትና ዕድገት ጉዞ ለማፋጠን የሚያስችሉ የ"ስማርት'' ከተሞችን ለመፍጠር ልምድ የሚወሰድበት ሃሳቦችን የያዘ መሆኑንም ገልጸዋል።   በአጠቃላይ የክልሉ መንግስት ከተሞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ ታግዘው አገልግሎትና ልማታቸውን እንዲያፋጥኑ የተለያዩ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን አስረድተዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው፤ መፅሐፉ ባለፉት አራት ዓመታት በከተማዋ ተግባራዊ የተደረገውን የስማርት አዳማ ኢንሼቲቭ ወደ ቀጣይ ምዕራፍ ለማሻገር የሚያግዙ ጠንካራ ሀሳቦች የያዘ ሰነድ ነው ብለዋል።   ባለፉት ዓመታት የስማርት አዳማ ግቦችን ለማሳካት የመሬት ሀብት አስተዳደርና አጠቃቀምን በማዘመን ሀብቱን ከምዝበራ መታደግ መቻሉን አክለዋል። የአገልግሎት አሰጣጥን በዲጂታል ቴክኖሎጂ በመምራት ማዘመን ችለናል ያሉት ከንቲባው፤ በዚህም የህብረተሰቡን የአገልግሎት እርካታ ከማሳደግ ባለፈ ብልሹ አሰራር መቀነስ ችለናል ብለዋል። "ኢንተርፕሪነሮችን" ለማፍራት፣ ክህሎት መር የስራ ዕድል ፈጠራና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በተደረገው ጥረት አበረታች ውጤቶች መገኘታቸውን አንስተዋል ። ዛሬ የተመረቀው መፅሐፍ የስማርት አዳማ ግቦችን ውጤታማ ጉዞ የቃኘ ከመሆኑም ባለፈ ከተማዋ በቀጣይ በሁለንተናዊ መልኩ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ልማትና ዕድገት ላይ የተሻለ ለመስራት አጋዥ እንደሚሆን ገልጸዋል። በመፅሐፉ ዝግጅት የኢትዮጵያ አርተፊሻል ኢንተለጀንስ ኢኒስቲትዩት፣ ኢትዮ ቴሌኮም፣ አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ፣ ኦሮሚያ ስቴትስ ዩኒቨርሲቲና የዘርፉ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል። በተመሳሳይ ፈጣን የትራንስፖርት አገልግሎት መስጠት የሚያስችሉ ዘጠኝ የከተማ አውቶብሶች ዛሬ አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል።   በዚህም አዳማ ከተማ አስተዳደር ስር መተዳደር የጀመሩ አዳዲስ ወረዳዎች ጭምር ቀልጣፋ የትራንስፖርት አገልግሎት በአነስተኛ ዋጋ እንዲያገኙ የሚያስችል ከመሆኑም ባለፈ የትራንስፖርት እጥረትን የሚቀንስ መሆኑ ተገልጿል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም