ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ወጣቱ በሳል የሆነ የማኀበራዊ ሚዲያ አጠቃቀምን መከተል ይገባዋል - ወጣቶች
Mar 27, 2025 42
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፡- ወጣቱ በሳል የሆነ የማኀበራዊ ሚዲያ አጠቃቀምን በመከተል እንደሚገባው ኢዜአ ያነጋገራቸው ወጣቶች ገለጹ። ማህበራዊ ሚዲያ የሰው ልጅን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ እንዲሁም አኗኗር ቀላል እያደረገው መጥቷል። በአዲስ አበባ ኢዜአ ያነጋገራቸው ወጣቶች ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የሚወጡ መረጃዎችን በሙሉ ከመውሰድ ይልቅ አጣርቶ መጠቀም ይገባል ይላሉ። ወጣት ህይወት አምባው እንዳለችው፤ አንዳንድ ማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች የተለያየ ዓላማን በመያዝ ሀሰተኛ መረጃዎችን ሲያሰራጩ ይስተዋላል። በመሆኑም መረጃዎቹን ከመጠቀም በፊት ትክክለኛነታቸውን ማጣራት ይገባል ብላለች። ወጣት ህይወት በማህበራዊ ሚዲያ የሚለቀቁ መረጃዎች ምንጫቸው ከየት ነው? ትክክለኛነቱስ ምን ያህል ነው? የሚለውን ማጤን ይገባልም ስትል ትመክራለች። ወጣቶች ትክክለኛ መረጃዎችን ከትክክለኛ ምንጮች በመውሰድ ራሳችንን ከሀሰተኛ መረጃ ከመጠበቅ ባለፈ ለህዝቦች አብሮነት መስራት አለብን ብላለች። ወጣቶች ማህበራዊ ሚዲያን ለምን ዓላማ ነው የምንጠቀመው የሚለውን ቆም ብለን ልናስብ ይገባል ያለው ደግሞ ወጣት ሃይለማሪያም ተሰማ ነው። የወጣቱ ማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም ብስለት የተሞላበት ሊሆን እንደሚገባና ሚዲያውን ለበጎ ነገር መጠቀም ይገባል ብሏል። በማህበራዊ ሚዲያ በርካታ ተከታዮችን ማፍራት መቻሉን የጠቀሰው ወጣት በረከት ከበደ በበኩሉ በማህበራዊ ሚዲያው የሚያስተላልፈውን መልዕክት ለሀገርና ለሕዝብ ምን ያህል ይጠቅማል የሚለውን የመመዘን ልምድ እንዳለው ገልጿል። በማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀም ላይ ያለውን ልምድ ለወጣቶች በማካፈል የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ መሆኑንም ነው የጠቆመው። ወጣት መንበረ መልኬ በበኩሉ ወጣቱ ማህበራዊ ሚዲያን በመጠቀም ለሀገር የሚጠቅም ገንቢ ሚና እንዲጫወት ግንዛቤን የማስፋት ሥራ ሊጠናከር ይገባል ብሏል። ለዚህም ባለድርሻ አካላት የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን መስጠት ላይ በልዩ ትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ በመጠቆም።
ሴቶች በሳይንስ ፣ ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ዘርፍ የግንባር ቀደምትነት ሚናቸውን ሊወጡ ይገባል
Mar 26, 2025 62
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፦ ሴቶች በሳይንስ ፣ ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ዘርፍ የግንባር ቀደምትነት ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ሴቶች የሳይንስና ቴክኖሎጂ ማህበር (SEWIST) 6ኛ ዓመታዊ ጉባኤ ተካሂዷል።   ጉባኤው የተካሄደው "የወደፊቱን የሚመሩ ሴቶች፤ የሴት ተመራማሪዎችን በሳይንስ፣በቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ማብቃት" በሚል መሪ ሀሳብ ነው። የማህበሩ ጉባዔ ሴቶችን በሳይንስ፣ቴክኖሎጂ ፣ፈጠራና ምርምር እድገት ያላቸው ሚና፣ ያሉ እድሎች እና ተግዳሮቶች ላይ ያተኮረ ነው። ሚኒስትር ዴኤታው በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ሴቶች በሳይንሳዊ ግኝቶች፣ በቴክኖሎጂ እድገት እና በፈጠራ መፍትሄዎች ግንባር ቀደም ሚና ሊወጡ ይገባል። በሳይንስ፣ቴክኖሎጂ፣ ኢንጂነሪንግ እና ሒሳብ /STEM/ ዘርፎች የሴት ምሁራን ሚና ወሳኝ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው በተለያዩ ጉዳዮች ላይ መፍትሄ ለማምጣት ሴቶችን ያሳተፈ ስራ ማከናወን እንደሚያስፈልግም አመልክተዋል። ማህበሩ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች እና የምርምር ተቋማት ጋር ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር በትኩረት እንደሚሰራም አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ሴቶች የሳይንስና ቴክኖሎጂ ማህበር ፕሬዝዳንት ሄለን ንጉሤ(ዶ/ር ) ኢትዮጵያ በሳይንስ፣ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን በርካታ ስራዎች እየሰራች እንደምትገኝ ገልጸዋል። በዘርፎቹ የተሟላ ውጤት ለማምጣት የሴቶች ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው ለዚህም በሳይንስ፣ቴክኖሎጂ፣ ኢንጂነሪንግና ሒሳብ /STEM/ ዘርፎች ያላቸውን አቅም መጠቀም እንደሚገባ አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ሴቶች በሳይንስና ቴክኖሎጂ ማህበር በ2014 ዓ.ም የተቋቋመ እና በሳይንስ ፣ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ላይ ትኩረት አድርጎ እንደሚሰራ ሚኒስቴሩ በመረጃው አመልክቷል።
የኢትዮጵያ የዲጂታል መሰረተ ልማት ግንባታ ለአፍሪካ ሀገራት ትምህርት ይሆናል
Mar 26, 2025 83
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ሀገራት ትምህርት የሚሆን የዲጂታል ኢኮኖሚና መሰረተ ልማት እየገነባች መሆኑን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የፈጠራና ቴክኖሎጂ ክፍል ኃላፊ ማክታር ሳክ(ዶ/ር) ገልጸዋል። ኃላፊው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአፍሪካ ሀገራት ጠንካራ የዲጂታል ፖሊሲ በመዘርጋት የከተማና ገጠር የቴክኖሎጂ ትስስርን በማስፋፋት በቁርጠኝነት መስራት ይጠበቅባቸዋል። ኢትዮጵያ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ በሰጠችው ትኩረት በስራ ዕድል ፈጠራና በኢንቨስትመንት ፍሰት እመርታዊ ለውጥ እያስመዘገበች እንደምትገኝ ገልጸዋል። መንግሥት ለዲጂታላይዜሽን በሰጠው ትኩረት የኢንተርኔት መሰረተ ልማት ተደራሽነት በሀገሪቱ በእጅጉ መስፋፋቱን አድንቀዋል። ጠንካራ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ የአሰራር ማዕቀፍ በማዘጋጀት የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነትን ማቀላጠፍ እንደሚያስፈልግም አጽንኦት ሰጥተዋል። የበይነ መረብ ግንኙነት ዕድገትም ለአህጉሪቱ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት መሳካት ወሳኝ በመሆኑ ለአፍሪካውያን ተመጣጣኝ አገልግሎት ማቅረብ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ከዚህ አኳያ ኢትዮጵያ በዲጂታል መሰረተ ልማትና ኢኮኖሚ ግንባታ ለአፍሪካውያን ትምህርት የሚሆን ስኬት እያስመዘገበች ነው ብለዋል።   የቴክኖሎጂ ንግድ ልማትና ግብይት ባለሙያ የሆኑት ሰርጌይ ጋስፓርያን በበኩላቸው፤ የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት የሀገር ውስጥ ገቢ የመሰብሰብ አቅምን ለማሳደግ ወሳኝ ነው ብለዋል። ዲጂታላይዜሽን የፋይናንስ አስተዳደርንና የታክስ የመሰብሰብ ሂደትን በማቀላጠፍ ግልጽነት ያለው የገቢና ወጪ ሥርዓት ለመፍጠር ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸዋል። ኢትዮጵያም የአምስት ዓመታት የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስትራቴጂ በመቅረጽ ባለፉት ዓመታት ያከናወነቻቸው ተግባራት የሚደነቁ ናቸው ብለዋል። በቀጣይም ከዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ምርትና አገልግሎት ሰጪዎች ጋር በመተባበር የዕውቀትና ክህሎት ሽግግር ላይ በትኩረት መስራት እንደሚገባም አንስተዋል። ኢትዮጵያ የመንግስትን የመፈጸም አቅም በማሳደግ ጠንካራ የኢኮኖሚ ዕድገት በመፍጠር አስደናቂ የልማት እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኗንም ጠቅሰዋል።
ዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂ ኤክስፖ በዲጂታላይዜሽን እና በቴክኖሎጂ የተመዘገቡ ውጤቶችን ለዓለም ማስተዋወቅና ትስስር መፍጠር ያስችላል
Mar 26, 2025 74
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- ዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂ ኤክስፖ 2025 በኢትዮጵያ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና በቴክኖሎጂ የተመዘገቡ ውጤቶችን ለዓለም የሚያስተዋውቅ እና ትስስር የሚፈጥር መሆኑ ተገልጿል፡፡ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ እና የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር) በጋራ የሚያዘጋጁትን ኤክስፖ በተመለከተ በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ እንደገለጹት፤ ዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂ ኤክስፖ 2025 ከግንቦት 8 ቀን ጀምሮ ለሶስት ቀናት በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ይካሄዳል፡፡   ኤክስፖው ኢትዮጵያ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ያስመዘገበቻቸው ስኬቶችን እና በዲጂታል ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤቶችን ለዓለም ለማስተዋወቅ ያለመ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ኤክስፖው የሳይበር ደህንነት፣ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የፋይናንስ ደህንነት፣ ስማርት ሲቲ እና የቴክኖሎጂ ትምህርት ትኩረት የሚያደርግባቸው መስኮች መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም ከ10 ሺህ በላይ ተሳታፊዎች፣ ከ100 በላይ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች እንዲሁም ከ50 በላይ ስታርታፖች ምርትና አገልግሎታቸውን የሚያስተዋውቁበት መድረክ መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል፡፡ ኤክስፖው ከ20 በላይ ጥናቶች፣ የፓናል ውይይቶች እንዲሁም የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሮቦቲክስ ውድድሮች የሚካሄዱበት መድረክ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ ስለሆነም በኢትዮጵያ የተሰናዳው ዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂ ኤክስፖ 2025 በተሳታፊም ሆነ በትኩረት መስኩ የምስራቅ አፍሪካ ትልቁ የቴክኖሎጂ ሁነት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኤክስፖው ከአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 የዲጂታላይዜሽን ጉዞ ጋር የተጣጣመ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂ ኤክስፖ 2025 በሰው ሰራሽ አስተውሎትና በሌሎች የቴክኖሎጂ መስኮች የተመዘገቡ ስኬቶቿን ለዓለም የምታስተዋውቅበት፣ ከሌሎች ልምድ የምትቀስምበትና ትስስር የምትፈጥርበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ከቅንጦት ይልቅ በሽታን በመከላከል፣ ትምህርትን በማስፋፋትና ድህነትን በመቀነስ ለሰው ልጅ መሰረታዊ ጉዳይ እየሆነ መምጣቱን አንስተዋል፡፡ በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ታዳጊ ሀገራት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ከድህነት ለመውጣት ለሚደረገው ጥረት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል፡፡ በተለይም የግሉ የቴክኖሎጂ ተዋንያን በስፋት እንዲሳተፉ በማድረግ በሰው ሰራሽ አስተውሎትና በሌሎች የቴክኖሎጂ ዘርፎች ልምድ የሚለዋወጡበትን አውድ ይፈጠራል ብለዋል።
የከተሞቹን መልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት በቴክኖሎጂ የተደገፈ አገልግሎት እየተሰጠ ነው
Mar 26, 2025 89
አዳማ፤ መጋቢት 17/2017 (ኢዜአ፦ በድሬዳዋና አዳማ ከተሞች የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት በቴክኖሎጂ የተደገፈ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን የከተሞቹ የስራ ሀላፊዎች ገለጹ። የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሃላፊ አቶ ገበየሁ ጥላሁን፤ የከተማው ነዋሪ የሚፈልገውን አገልግሎት እንዲያገኝ በቴክኖሎጂ የመደገፍ ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በዚህም ከድሬዳዋ አስተዳድር ሳይንስና ቴክኖሎጂ ቢሮ ጋር በመሆን አገልግሎቱን ወደ ዲጂታል የመቀየርና ተገልጋዩ ካለበት ሆኖ የተሻለና ፈጣን አገልግሎት ማግኘት እንዲችል እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል። በተለይም ከመሬት አስተዳደር፣ ከገቢዎች፣ ከከተማ ፀጥታና ደህንነት ጋር በተያየዘ እንዲሁም የዕለት ተዕለት የህዝብ አገልግሎት የሚበዛባቸው የአስተዳደሩ ሴክተር ተቋማት አገልግሎቶችን የማዘመን ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በእነዚሁ ተቋማት በአንድ ማዕከል አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉን ጠቅሰው፤ ይህም ሌብነትና ብልሹ አሰራርንም ለመከላከል እያገዘ ነው ብለዋል። በተጨማሪም ነዋሪዎች ካሉበት ሆነው የንግድ ፍቃድ እንዲያድሱና የግንባታ ፍቃድ እንዲያገኙ በማድረግ አገልግሎቱን ማሳለጥ መቻሉን ጠቅሰው፤ በዚህም የከተማውን የሰላም ሁኔታ አስተማማኝ ማድረግ አስችሏል ብለዋል። በተመሳሳይ የአዳማ ከተማ የስራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ፉፋ ገርማማ በበኩላቸው በከተማዋ አገልግሎቶችን በማዘመንና ዲጂታል በማድረግ ተገልጋይ ሳይቸገር የሚፈልገውን አገልግሎት እንዲያገኝ መደረጉን ተናግረዋል። በከተማዋ ተገልጋዮች ካሉበት ሆነው ሳይንገላቱ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን ጠቅሰው፤ በተለይም 'ጋዲሳ ኦዳ' በሚል የአንድ ማዕከል አገልግሎት መሰጠቱ የተሻለ ውጤት እይስገኘ መሆኑን አስረድተዋል። ይህም አብዛኛው ተቋማት አንድ ቦታ ሆነው የተቀናጀና የተናበበ አገልግሎት በመስጠት የህዝብ ቅሬታን ደረጃ በደረጃ መፍታት ማስቻሉን አመልክተዋል። በአሁኑ ወቅት የስራ አጥ ወጣቶች ምዝገባ ዲጂታል ከማድረግ ባለፈ በስማርት ሴኩሪቲ የከተማዋን ሰላምና ፀጥታ ሁኔታዎችን የመከታተል፣ የመሬትና መሬት ነክ አገልግሎቶችንም ከወረቀት ንኪኪ ነፃ የማድረግ ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። ዲጂታል አገልግሎቱ ተገልጋዩ የትራፊክ ፍሰት ቁጥጥር፣ የትራንስፖርት ስምሪትና የትራፍክ ቅጣት ክፍያ አሽከርካሪዎች ካሉበት ሆነው በተንቀሳቀሽ ስልክ እንዲከፍሉ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency
ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ኤክስፖ 2025 በመጪው ግንቦት ወር በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Mar 26, 2025 81
አዲስ አበባ፤መጋቢት 17/2017 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ዓለም አቀፍ ኤክስፖ 2025 ከመጪው ግንቦት 8 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ለሶስት ቀናት በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ይካሄዳል። በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር እና በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የሚዘጋጀው ኤክስፖ በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ የቴክኖሎጂ ሁነት መሆኑ ተገልጿል። ኤክስፖውን በተመለከተ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ እና የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ እንዳሉት፤ ኤክስፖው ኢትዮጵያ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ያስመዘገበቻቸው ስኬቶችን ለዓለም ለማስተዋወቅ ያለመ ነው። በኢትዮጵያ የትራንስፎርሜሽን ዲጂታል ኢኮኖሚን በማሳለጥ የበለጸገ ማህበረሰብና ሀገር ለመፍጠር በተከናወኑ ተግባራት አመርቂ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል። የተቀናጀ እና ወጪ ቆጣቢ የዲጂታል ቴክኖሎጂ በመገንባት ሂደት የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ገንቢ ሚና መጫወቱን ገልጸዋል፡፡ የሳይበር ደህንነት፣አርቲፊሻል ኢንተሊጀንስ፣ የፋይናንስ ደህንነት፣ ስማርት ሲቲ እና የቴክኖሎጂ ትምህርት በኤክስፓው የትኩረት ነጥቦች መሆናቸውን ተናግረዋል። እነዚህን አምስት የትኩረት መስኮች በአንድ ላይ የያዘ ኤክስፖ በመሆኑ በምስራቅ አፍሪካ ትልቁ የቴክኖሎጂ ሁነት ያደርገዋል ብለዋል። በኤክስፓው ከ10 ሺህ በላይ ተሳታፊዎች እንደሚጠበቁ ገልጸው፣ የጎንዮሽ ስብሰባዎች፣ ኤግዚቪሽን፣ ሲምፖዚየም እና ውድድሮች የሚካሄዱበት መሆኑን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና በበኩላቸው፣ ኤክስፖው ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂዋን በዓለም የምታስተዋውቅበት፣ እንዲሁም ከዓለም የምትማርበት የቴክኖሎጂ መድረክ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የግሉ የቴክኖሎጂ ዘርፍ ተዋንያን በስፋት እንዲሳተፉ በማድረግ በዘርፉ ልምድ የሚለዋወጡበትን አውድ ይፈጠራል ብለዋል። ኤክስፖው ከአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 የዲጂታላይዜሽን ጉዞ ጋር የተጣጣመ መሆኑን ገልጸው፣ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ውድድር እንደሚደረግም ተናግረዋል።
ኢትዮ ቴሌኮም እና ማስተርካርድ የዲጂታል የፋይናንስ አገልግሎቶችን በጋራ ማሻሻል የሚያስችል ስትራቴጂያዊ ውይይት አደረጉ   
Mar 25, 2025 62
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ እና የማስተርካርድ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ማርክ ኤሊዮት በኢትዮጵያ አዳዲስ የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎቶችን ለማስጀመር የትብብር እድሎችን መፈተሽ የሚያስችል ውይይት አካሂደዋል። በውይይቱ የሁለቱ ተቋማት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎችም መሳተፋቸውን ከኢትዮቴሌኮም የተገኘው መረጃ ያመላክታል። ተቋማቱ የመከሩበት የትብብር ማዕቀፍ የቴሌብርን እና የማስተር ካርድን ፕላትፎርሞች በመጠቀም የዲጂታል ፋይናንስ ሶሉሽኖችን ለማሳደግ፣ የፋይናንስ ተደራሽነትን በከፍተኛ ሁኔታ ለማስፋት እና ዘላቂ እድገትን ለማበረታታት ያለመ መሆኑም ተገልጿል። የኢትዮቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ተቋማቸው በአፍሪካ ትልቅ የደንበኞች ቁጥር እና ግዙፍ መሠረተ ልማት ያለው በመሆኑ ይህም አዳዲስ እድሎችን ለመክፈት አስቻይ ሁኔታ እንደፈጠረለት አብራርተዋል።   በዚህም ከማስተርካርድ ጋር በአጋርነት ለመስራት ያላቸውን ተነሳሽነት አረጋግጠዋል። የማስተርካርድ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ማርክ ኤሊዮት በበኩላቸው የኢትዮቴሌኮም ፈጣን የደንበኞች ቁጥር ዕድገት እና ግዙፍ የመሰረተ ልማት አቅም ለአጋርነት ተመራጭ እንደሚያደርገው ተናግረዋል። ለማስተርካርድም ይህ ትብብር መልካም አጋጣሚ የፈጠረለት መሆኑንና ለተግባራዊነቱ ቁርጠኛ መሆናቸውንም አረጋግጠዋል። ይህ ስትራቴጂያዊ ትብብር ኢትዮጵያን በዓለም የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ ያላትን ተወዳዳሪነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያሳድግም በመረጃው ተጠቁሟል። ይህም ዘላቂ ዕድገትንና የሀብት ፈጠራን በማበረታታት አካታች እና ሁሉን አቀፍ የዲጂታል ፋይናንስ ምህዳር እንዲሁም ዘላቂ እድገት ለማስመዝገብ እንደሚያስችልም ተገልጿል።
ለዜጎች ሥራ ዕድል ፈጠራ ከግሉ ዘርፍ ጋር የሚከናወኑ የትብብር ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ- ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Mar 25, 2025 76
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2017(ኢዜአ)፦ ለዜጎች ሥራ ዕድል ፈጠራ ከግሉ ዘርፍ ጋር የሚከናወኑ የትብብር ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና ሀይብሪድ ዲዛይን (ራይድ) በፈጠራ፣ በሥራ ዕድል እና በክህሎት ልማት ላይ በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር የሚያስችል እና ለአምስት ዓመታት የሚቆይ መሆኑ ተገልጿል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ መንግስት ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር እየሰራ ነው።   በዚህ ሂደት የግሉ ዘርፍ ያለው ሚና አይተኬ በመሆኑ ሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ በትብብር የሚከናወኑ ተግባራት መኖራቸውን ነው ያብራሩት። ከሀይብሪድ ዲዛይን ጋር የተደረሰው የመግባቢያ ስምምነት በቴክኖሎጂ ዘርፍ ለበርካታ ወጣቶች፣ ሴቶችና አካል ጉዳተኞች የስራ ዕድል ለመፍጠር የሚያስችል እንደሆነም ጠቁመዋል። የሀይብሪድ ዲዛይን (ራይድ) መስራችና ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሳምራዊት ፍቅሩ በበኩላቸው፥ ድርጅታቸው በትራንስፖርት ቴክኖሎጂ ዘርፍ በመቶ ሺዎች ለሚቆጠሩ ዜጎች የሥራ ዕድል እየፈጠረ መሆኑን ገልፀዋል።   ስምምነቱ የቴክኖሎጂ ትራንስፖርት አገልግሎት ዘርፍ ለሥራ ዕድል ፈጠራ ያለውን አስተዋፅዖ ለማሳደግ ያለመ ነው ብለዋል። በዚህም መሰረት ሀይብሪድ ዲዛይን ከራይድ ውጭ ሌሎች ፕሮጀክቶችን በመንደፍ ለበርካታ ለዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ጠቅሰዋል።
ከ 580 ሺህ በላይ ዜጎች የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ስልጠናን በመከታተል ላይ ናቸው
Mar 25, 2025 88
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 16/2017(ኢዜአ)፦በአገር አቀፍ ደረጃ ከ 580 ሺህ በላይ ዜጎች የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ስልጠናን በመከታተል ላይ መሆናቸውን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። ስልጠናውን ያጠናቀቁ ከ180 ሺህ በላይ የሚሆኑ ዜጎች የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ሚኒስቴሩ አስታውቋል። መርኃ ግብሩ በኢትዮጵያ መንግስትና በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች እገዛ የሚተገበር የዲጂታል ሥራ ክህሎት ማሳደጊያ የትብብር ፕሮጀክት ነው። ፕሮጀክቱ "ትውልድ ይማር፣ ትውልድ ይሰልጥን፣ ከዓለም ጋር ይፎካከር" በሚል እሳቤ ዜጎች የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማዳበር በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ብቁ እንዲሆኑ እየተተገበረ ይገኛል፡፡ ፕሮጀክቱ በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት አምስት ሚሊየን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት እንዲጨብጡ የሚያስችል ነው። በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የአይሲቲና ዲጂታል ኢኮኖሚ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ይሹሩን አለማየሁ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤መርኃ ግብሩ የዲጂታል ክህሎትን ለመገንባት የሚያስችል ነው። በመርኃ ግብሩ ከ 580 ሺህ በላይ ዜጎች ተመዝግበው ስልጠና እየተከታተሉ ሲሆን ከእነዚህም መካከል 180 ሺህ የሚሆኑት የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። በአዲስ አበባ፣ ድሬዳዋና ሐረር የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ስልጠና አፈፃፀም የተሻለ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ መርኃ ግብሩን የተሳካ ለማድረግ ሌሎች ክልሎች በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበው ሚኒስቴሩም አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልፀዋል። ስልጠናው የፈጠራ ስራን ለማበረታታት የሚያግዝ በመሆኑ በተለይ ወጣቶች ይህን እድል ተጠቅመው ራሳቸውን ማብቃት እንዳለባቸው አስረድተዋል።  
የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር የጀመረው በቴክኖሎጂ የተደገፈ የክፍያ ስርዓት ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ እያስቻለን ነው - ተጠቃሚዎች
Mar 22, 2025 191
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 13/2017(ኢዜአ)፡- የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር የጀመረው በቴክኖሎጂ የተደገፈ የክፍያ ስርዓት ቀልጣፋ እና ዘመናዊ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል ሲሉ የባቡር ትራንስፖርት ተጠቃሚዎች ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ቀላል ባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት በተመረጡ የባቡር ጣቢያዎች የዲጂታል ትኬት አገልግሎት መስጠት ጀምሯል፡፡ ከዲጂታል ትኬት አገልግሎት ተጠቃሚዎች መካከል ወጣት መብራቴ ደረጀ ለኢዜአ እንዳለው፤ ዲጂታል የክፍያ ሥርዓት ተግባራዊ መደረጉ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘት አስችሏል፡፡ የዲጂታል የክፍያ ሥርዓት እንግልትን የሚያስቀርና ጊዜውን የዋጀ አገልግሎት መሆኑን ገልፆ፤ አሰራሩን ሙሉ በመሉ ለመተግበር ለማህበረሰቡ ግንዛቤ መፍጠር እንደሚገባ ተናግሯል። የዲጂታል የክፍያ ሥርዓት ጊዜን በመቆጠብ ቀልጣፋና ፈጣን አገልግሎት መሥጠት የሚያስችል በመሆኑ በሁሉም አካባቢዎች ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የገለጸው ደግሞ መምህር ዮርዳኖስ ወልደአማኑኤል ነው፡፡ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ወጣት ኪሶ ጋሩማ አገልግሎቱ በአንድ ትኬት ከሁለት ጊዜ በላይ የሚጠቀሙ ሰዎችን በማስቆም ብልሹ አሰራርን መቆጣጠር ያስችላዋል ብሏል፡፡ የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት ዋና ሥራ አሥፈጻሚ ብርሃነ አበባው(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የባቡር ትራንስፖርት የትኬት አገልግሎት በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግ የሙከራ ሥራ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡ የወረቀት ትኬት ስርዓት የመዲናዋን የባቡር ትራንስፖርት አገልግሎት የማይመጥን መሆኑን ገልጸው፤ ስርዓቱ የተሳለጠ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችልም ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር በ19 ባቡሮች ለህብረተሰቡ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ በበጀት ዓመቱ መጨረሻ 21 ለማድረስ እቅድ ተይዟል ብለዋል፡፡
በጋምቤላ ክልል የኮደርስ ዲጂታል ስልጠና አፈጻጸምን ለማጠናከር በትኩረት መስራት ይገባል - ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር)
Mar 21, 2025 124
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2017(ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል በኮደርስ ዲጂታል ስልጠና የተሻለ አፈጻጸም ለማስመዝገብ በትኩረት መስራት እንደሚገባ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን(ዶ/ር) አስገነዘቡ። የክልሉ የ5 ሚሊዮን የኢትዮጵያ ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ፕሮግራም አፈጻጸም ተገምግሟል። ፕሮግራሙ በጋምቤላ ክልል መስከረም 24 ቀን 2017 ዓ.ም መጀመሩ ይታወሳል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን(ዶ/ር) በክልሉ በሶስት ዓመት ውስጥ 47 ሺህ 287 ሰዎች ስልጠናውን እንዲወስዱ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል። በመጀመሪያው ዓመት 11ሺህ 822 ተሳታፊዎች ስልጠናውን እንዲከታተሉ ግብ መቀመጡንም አመልክተዋል። ይሁንና አፈጻጸሙ በሚፈለገው ደረጃ ላይ እንደማይገኝና ይህንን ለማሻሻል አመራሮች እና ባለድርሻ አካላት የጋራ ርብርብ እንዲያደርጉ አሳስበዋል። በቀጣይ ሰፊ ቅስቀሳና ንቅናቄ በማድረግ፣ የቅንጅት አሰራርንና ክትትልን በማጠናከር እንዲሁም በግንዛቤ ፈጠራ በተሻለ መልኩ ማከናወን እንደሚገባ አቅጣጫ መቀመጡን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያን እድገት እና ልማት የሚያፋጥኑ የምርምር ስራዎችን የመጠቀም አቅም ማሳደግ ይገባል - የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር
Mar 20, 2025 94
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 11/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን እድገት እና ልማት የሚያፋጥኑ የምርምር ስራዎችን የመጠቀም አቅም ማጠናከር እንደሚገባ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) ገለጹ። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ኦስትሪያ ከሚገኘው "International Institute for Applied Systems Analysis" ተቋም ጋር በበይነ መረብ ውይይት አድርጓል። ውይይቱ የኢትዮጵያን ሀገራዊ አጀንዳ የሚደግፉ የጋራ ምርምር፣ የዕውቀት ሽግግር እና የአቅም ግንባታ ጥረቶች እድሎችን ለመለየት፣ ግንኙነት ለማጠናከርና ቀጣይ እርምጃዎችን ለማስቀመጥ ያለመ ነው። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) ኢትዮጵያ እድገትንና ልማትን ለማፋጠን በምርምር የተደገፈ ኢንቨስትመንት እና አዳዲስ ፈጠራዎችን ወደ ገበያ ለማሸጋገር እየሰራች እንደሆነ ገልፀዋል። በዚህ ረገድም ኢትዮጵያ ከሰሃራ በታች ካሉ የአፍሪካ ክልላዊ አባል ሀገራት ንቁ ተሳታፊ መሆኗንም ተናግረዋል። የ10 ዓመት የልማት እቅድ(2021-2030) እና የኢኮኖሚ ማሻሻያዎቹ ሳይንስ፣ ፈጠራ እና ቴክኖሎጂ የዘላቂ ልማት ወሳኝ አንቀሳቃሾች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያን እድገት እና ልማት የሚያፋጥኑ የምርምር ስራዎችን የመጠቀም አቅም ማሳደግ እንደሚገባም ተናግረዋል። በውይይቱ ሁለቱ ወገኖች ችግሮችን መፍታት የሚያስችሉ አዳዲስ መፍትሄዎችን፣ ውጤቶችን ለማምጣት የትብብር ቁልፍ ጉዳዮችን በመለየት በቀጣይ የመግባቢያ ስምምነት ሰነድ ለማዘጋጀት እና ወደ ስራ ለመግባት መስማማታቸውን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በኢትዮጵያ የታካሚዎች የሜዲካል ቦርድ የዲጂታል ሰርተፊኬት አገልግሎት ተጀመረ
Mar 19, 2025 116
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 10/2017(ኢዜአ):- የጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በኢትዮጵያ መጀመሪያ የሆነውን የታካሚዎች የሜዲካል ቦርድ የዲጂታል ሰርተፊኬት አገልግሎትን ዛሬ በይፋ አስጀምሯል። ሰርተፍኬቱ በወረቀት ሲሰጥ የነበረውን የታካሚዎች ሜዲካል ቦርድ አሰራር የሚያስቀር ነው።   የጤና ሚኒስትር ዴኤታ እና የጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ የአገልግሎቱ መጀመር ወደ ውጭ ሀገር ሄደው ህክምና ለሚፈልጉ ታካሚዎች እንግልት የሚቀንስና የአገልግሎት ፈላጊዎችን እርካታ የሚጨምር መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የሆስፒታሉን የአገልግሎት አሰጣጥ ይበልጥ የሚያሻሽል እንዲሁም የተሳሳቱ ማስረጃዎችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር አጋዥ እንደሆነ አመልክተዋል።   ሚኒስትር ዴኤታው አክለውም የጤና ሚኒስቴር ወደ ውጭ ሀገር ሄደው ህክምና ለሚፈልጉ ታካሚዎች ወጥ በሆነ አሰራር ማስተናገድ የሚያስችል መመሪያ እያዘጋጀ መሆኑንም ጠቁመዋል። የሆስፒታሉ ሁሉንም አገልግሎቶች ዲጂታላይዝ ለማድረግ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ አሳስበው ለዚህም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ለሆስፒታሉ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚጠቀጥል ተናግረዋል።   የጥቁር አንበሳ ስፔሻላይድ ሆስፒታል ቺፍ ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አንዱዓለም ደነቀ ሆስፒታሉ የታካሚዎች የሜዲካል ቦርድ የዲጂታል ሰርተፊኬት አገልግሎት መስጠት መጀመሩ የተገልጋዮችን እርካታ እንደሚጨምር ገልጸዋል። አገልግሎቱ የተጀመሩ የሜዲካል ሪከርድ ስርዓትን የበለጠ ለማጠናከር እንደሚያግዝም አመልክተዋል። የዲጂታል ሰርተፍኬቱ ስራ ሌሎች ሆስፒታሎች እና የጤና ተቋማት አገልግሎቱን እንዲጀምሩ በር ከፋች መሆኑንም ገልጸዋል።   በተጨማሪም ማሪ ስቶፕስ ኢትዮጵያ ለጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ከመወለጃ ቀናቸው አስቀድሞ ለሚወለዱ ጨቅላ ህፃናት ክብካቤ የሚያገለግሉ የህክምና ቁሳቁስ እንዲሁም ለማወለጃ ክፍል እድሳት የሚሆን ከሁለት ሚሊየን ብር በላይ ድጋፍ አድርጓል። ዶክተር ደረጀ ድጋፉ የግል እና የመንግስት ተቋማት በትብብር መስራት እንደሚችሉ ማሳያ እንደሆነ መግለጻቸውን ከጤና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የፈጠራ ሃሳቦችን በስፋት ወደ ተግባር መለወጥ እንዲችሉ የሚደረገው ማበረታቻ መጠናከር አለበት - የፈጠራ ባለቤት ተማሪዎች
Mar 19, 2025 105
ባህርዳር፤ መጋቢት 10/2017(ኢዜአ)፡- የፈጠራ ሃሳቦቻቸውን በስፋት ወደ ተግባር በመለወጥ ለሀገር ጥቅም ማዋል እንዲችሉ የሚደረግላቸው የማበረታች ድጋፍ እንዲጠናከር በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፈጠራ ባለቤት ተማሪዎች ጠየቁ። በባህርዳር ከተማ በተካሄደው የወጣቶች የስራ ፈጠራ ውድድር ተሳታፊዎች መካከል በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ የአምስተኛ ዓመት የማቴሪያል ሳይንስና ምህንድስና ተማሪ ዮሐንስ ይታይ አንዱ ነው። ተማሪው ለኢዜአ በሰጠው አስተያየት፤ የቀለም ማጣበቂያ ምርት(paint binder production) ከጓደኞቹ ጋር በመሆን መፍጠር እንደቻሉ ተናግሯል። ውጤታማነቱ በቀለም ፋብሪካዎችና በዘርፉ ባለሙያዎች የተረጋገጠውን የፈጠራ ውጤት ሰሞኑን በተካሄደው ውድድር በማቅረብ 3ኛ በመውጣት ለሽልማት መብቃታቸውን ገልጿል። ይህ የፈጠራ ውጤት እገዛ ተደርጎልን በስፋት ወደ ማምረትና ማከፋፈል ቢሸጋገር ምርቱን ከውጭ ለማስገባት የሚወጣውን የውጭ ምንዛሬ በማስቀረት የሀገርን ኢኮኖሚ እድገት ለማፋጠን እንደሚያግዝ ጠቁሟል። በዚህም ለሀገር ወስጥ ፍጆታ የሚውል በቂ ምርት ለማምረት ፍላጎት ያላቸው በመሆኑ የሚመለከታቸው አካላት የመስሪያ ቦታና ብድር እንዲያመቻቹላቸው ጠይቋል። ወጣቶች የፈጠራ ሃሳቦቻቸውን ወደ ተግባር እንዲለውጡ እየተደረጉ ያሉ ድጋፎች አበረታች ናቸው ያለችው ደግም በዩኒቨርሲቲው የ5ኛ ዓመት የኬሚካል ምህንድስና ተማሪና የፈጠራ ባለቤት እፁብ ድንቅ ቦሩ ናት። አንድ የፈጠራ ስራ ችግር ፈቺነቱ የሚረጋገጠው በናሙና ደረጃ አዋጭ ሆኖ ስለተገኘ ብቻ ሳይሆን በስፋት ለተጠቃሚዎች ተደራሽ መሆን ሲችል መሆኑን በመገንዘብ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠይቃለች። የፈጠራ ሥራ የራስን አቅም የመጠቀም ልምድን በማዳበር ለቀጣይ የምርምር ሥራ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን የፈጠራ ባለቤት ተማሪዎቹ ጠቁመዋል። በባህርዳር ከተማ በተካሄደው የወጣቶች የስራ ፈጠራ ውድድር ላይ የተገኙት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ በመላው ኢትዮጵያ ፈጠራን በመደገፍና በማስተዋወቅ የሀገር በቀል ኢኮኖሚው እንዲበረታታ እየተሰራ መሆኑን መግለጻቸው ይታወሳል። ለዚህም በየአካባቢው የሚወጡ የወጣቶች የፈጠራ ስራን በመደገፍ፣ በማበረታታትና ለውጤት እንዲበቃ በማድረግ ለኢትዮጵያ ልማትና እድገት መፋጠን የተጀመረው ቅንጅታዊ አሰራር ተጠናክሮ ይቀጥላል ማለታቸውም እንዲሁ። በባህርዳር ከተማ ሰሞኑን የተካሄደውን የወጣቶች የስራ ፈጠራ ውድድር መዘገባችን የሚታወስ ነው።
የኮደርስ ስልጠናው የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ክህሎትን ያሳደገ ነው
Mar 19, 2025 94
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 10/2017(ኢዜአ)፦ የ5 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ስልጠና የቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎታቸውን በማላቅ በአለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የሚረዳቸው መሆኑን ስልጠናውን ተከታትለው ያጠናቀቁ ወጣቶች ገለጹ። ስልጠናው ለሚሰሩት ስራ ተጨማሪ አቅምን እንደሚፈጠረላቸውም ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐምሌ 16 ቀን 2016 ዓ.ም የአምስት ሚሊየን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ስልጠና ኤኒሼቲቭ ማስጀመራቸው ይታወሳል። ኤኒሼቲቩ "ትውልድ ይማር፣ ትውልድ ይሰልጥን፣ ከዓለም ጋር ይፎካከር" በሚል እሳቤ ወጣቶች የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማዳበር በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ብቁ ለማድረግ እየተተገበረ ይገኛል፡፡ ኤኒሼቲቩ በቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት 5 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት እንዲጨብጡ የሚያስችል ነው። ስልጠናውን ያጠናቀቁ ወጣቶች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተለዋዋጭ ሁኔታዎች ውስጥ ከሚፈጠሩ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ጋር ራሳቸውን በፍጥነት እንዲያራምዱ የኮደርስ ስልጠናው ወሳኝ ነው፡፡ ከስራዋ ጎን ለጎን አራቱንም ስልጠናዎች በማጠናቀቅ ምስክር ወረቀት ያገኘችው ትዕግስት ጉዱ እንዳለችው ስልጠናው ተወዳዳሪነትን የሚያሳድግ ነው። ስልጠናው ከፅሁፍ በተጨማሪ በምስል ተደግፎ መሰጠቱ ሳቢ እንደሚያደርገው የገለፀው ይድነቃቸው ተስፋዬ በበኩሉ በስልጠናው ያገኘው እውቀት ለሚሰራው ስራ ተጨማሪ አቅም መሆኑን ተናግሯል። ስልጠናው በአለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብት በመሆኑ እድሉን በመጠቀም ራስን ከዘመኑ ጋር ማዘመን ያስፈልጋል ብለዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሰለሞን አማረ በበኩላቸው በመዲናዋ በቀጣዮቹ ሶስት አመታት በአምስት ሚሊየን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ መርሃግብር 300ሺህ ነዋሪዎችን ለማብቃት ታቅዷል ብለዋል። ስልጠናው ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስከ የካቲት 30 ቀን 2017ዓ.ም ድረስ ከ165 ሺህ በላይ ወጣቶች ሥልጠናውን እየተከታተሉ ሲሆን 56 ሺህ ያህሉ ደግሞ ምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ስልጠናው የዲጂታል ክህሎትን በማበልጸግ ስማርት ሲቲን ለመፍጠር የሚያግዝ በመሆኑ በከተማዋ ከማዕከል እስከ ወረዳ ያሉ ቢሮዎች ሰራተኞቻቸው ስልጠናውን እንዲከታተሉ ማበረታታት እንዳለባቸው አስረድተዋል።
ኢትዮጵያ በራዲየሽንና ኒውክሌር ቴክኖሎጂ ቁጥጥር የካበተ ልምድ አዳብራለች - ባለስልጣኑ
Mar 19, 2025 105
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 10/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ በራዲየሽንና ኒውክሌር ቴክኖሎጂ ያካበተችውን ጠንካራ የቁጥጥር ስርዓት በተጨማሪ ቴክኖሎጂዎች ላይ ለመተግበር እየሰራች መሆኑን የኢትዮጵያ ቴክኖሎጂ ባለስልጣን ገለፀ። ባለስልጣኑ የፌደራል መንግስት አስፈፃሚ አካላትን ስልጣንና ተግባር ለመወሰን በወጣው አዋጅ ቁጥር 1263/2014 ተጨማሪ ተግባርና ኃላፊነት ተሰጥቶታል። በዚህም የኒውክሌር እና የጨረራ አመንጭ መሳሪያዎችና ቁሶች ወደ ሀገር ውስጥ ሲገቡ፤ ከሀገር ሲወጡ፤ ጥቅም ላይ ሲውሉ፤ ሲጓጓዙ፤ ሲወገዱ፤ ሲዘዋወሩ፤ ሲከማቹ፣ የቁጥጥር፤ ህግ የማስፈጸም እና የክትትል ተግባራትን ያከናውናል፡፡ ባለስልጣኑ በተሰጠው ስልጣን ከዚህ ቀደም ከሚቆጣጠራቸው የጨረራና ኒውክሌር ቴክኖሎጂ በተጨማሪ አራት ቴክኖሎጂዎችን የመቆጣጠር ስራ እየሰራ ይገኛል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ጌታቸው ለኢዜአ እንዳሉት ባለስልጣኑ ጨረር አመንጪዎችን የማሳወቅ፣ የፍቃድ አሰጣጥ፣ ኢንስፔክሽንና ህግ ማስፈፀም እንዲሁም በህግ ጥሰት ላይ እርምጃ የመውሰድ ስራ ሲያከናውን ቆይቷል። በዚህም ባለፉት ሰባት ወራት በሁሉም ቴክኖሎጂዎች 2ሺህ 657 የተለያዩ ፈቃዶች ለመስጠት አቅዶ 2ሺህ 422 ፈቃድ መስጠት መቻሉን ተናግረዋል። በተጨማሪም በሁሉም ቴክኖሎጂዎች 504 የኢንስፔክሽን ስራ እንዲሁም የማሳወቅና የመረጃ ምዝገባ ስራዎች መሰራታቸውንም አብራርተዋል። በህክምና እና ኢንዱስትሪ ዘርፍ የአገልግሎት ዘመንና የፕሮጀክት ጊዜያቸውን በጨረሱ ጨረራ አመንጪ ቁሶች ላይ የህግ ማስፈፀም ስራ ማከናወን መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም በተቋማቱ ላይ ከቀላል ማስጠንቀቂያ ጀምሮ የተለያዩ የህግ ማስፈፀም ስራዎች መሰራታቸውን ጠቁመው አንድ ድርጅት በፍርድ ቤት ውሳኔ አገልግሎቱን የጨረሰ ቴክኖሎጂ ወደ መጣበት ሀገር እንዲመልስ መደረጉንም ገልፀዋል። በራዲየሽንና ኒውክሌር ቴክኖሎጂ ላይ እየተከናወነ ያለውን ጠንካራ የቁጥጥር ስርዓት በሌሎች ቴክኖሎጂዎች ላይ ለመድገም የህግ ዝግጅት መከናወኑን አስታውቀዋል። ባለስልጣኑ የጨረራ ህክምና ምርምራ መስጫን ጨምሮ ጨረራ አመንጪ መሳሪያዎች ያለ ፈቃድ ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገቡ ለመቆጣጠር ከጉምሩክ ኮሚሽንና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
መገናኛ ብዙሃን በዲጂታል ዓለም ቁልፍ ተዋናይ ሊሆኑ ይገባል- ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት
Mar 18, 2025 89
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 9/2017 (ኢዜአ)፦ ዓለም ዲጂታል መልክ በያዘበት በዚህ ዘመን መገናኛ ብዙሃን የዘርፉ ቁልፍ ተዋናይ ሊሆኑ እንደሚገባ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ገለጹ። የአማርኛ ፌስቡክ ገጽ ተከታይ 4 ሚሊየን መሻገሩን ተከትሎ “ፋና ሚዲያ ዲጂታል ዐርበኛ” በሚል መሪ ሐሳብ የማበረታቻና ዕውቅና መርሐ ግብር ተካሂዷል። አማካሪ ሚኒስትሩና የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን የቦርድ ሰብሳቢ ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፣ የተቋሙ አመራሮች፣ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት፣ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን፣ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት እና የአዲስ ሚዲያ ኔትወርክ የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም የዲጂታል ሚዲያ ባለሙያዎች ተገኝተዋል።   አማካሪ ሚኒስትሩና የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን የቦርድ ሰብሳቢ ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በወቅቱ እንዳሉት ዓለም ወደ ዲጂታል በመለወጡ ሚዲያው በድሮ አሰራር ብቻ መቀጠል አይቻልም። የአዲሱ ትውልዱ ቋንቋ ወደ ዲጂታል ዓለም እየተለወጠ መምጣቱን ጠቅሰው፤ መገናኛ ብዙሃን ዲጂታል ዘርፍ በሁሉም ፕላትፎርሞች ተጠናክሮ መውጣት እንዳለበት አንስተዋል። ሚዲያ የነገ መልክ የሚቀርጽ በመሆኑ የዲጂታል ዓለም ውስጥ ዋኝቶ ለመሻገር በዘርፉ ቁልፍ ተዋናይ መሆን እንዳለበት ገልጸዋል። እንደ ሀገር የሚዲያዎችን የዲጂታል አቅም ለማጎልበት በሰው ኃይል የማብቃት፣ ተደራሽነትና የቴክኖሎጂ አቅምን የማሳደግ ስራ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን የማህበራዊ ሚዲያ ዘርፍ ተደራሽነትን ለማሳደግ በርካታ ስራዎች በመሰራቱ ዕውቅናው እንደተሰጠ ጠቅሰዋል። ኢዜአን ጨምሮ ባለፉት ወራት የዲጂታል አቅም ለማጎልበት ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመቀናጀት ሲሰራ መቆየቱን ገልጸው፤ ሁሉም ተቋማት በየፊናቸው በፈጣን ለውጥ ላይ መሆናቸውን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰይፈ ደርቤ የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዲጂታል ቡድን የሰራው ስራ ውጤታማ መሆኑን አንስተው፤ ከ4 ሚሊየን የተሻገረ ተከታይ በማፍራታችሁ እንኳን ደስ አላችህ ብለዋል። የሚዲያ ተቋማት ሕብረት ፈጥረው ፋና ላይ የመጣው ለውጥ ወደ ሌሎች ተቋማትም ሊስፋፋ እንደሚገባው አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጌትነት ታደሰ፤ የዲጂታል ሚዲያው ዘርፍ በሀገር ግንባታ ውስጥ የድርሻውን እንዲወጣ ሁሉም ሚናውን መጫወት እንዳለበት ጠቁመዋል። ሁሉንም ሚዲያ አማራጮችና አቅም በማሰባሰብ ጥሩ ውጤት እየመጣ እንደሆነም ገልጸው፤ እንደ ሚዲያ ብንፎካከርም የምንሰራው ለአንድ ሀገር መሆኑ መረሳት የለበትም ብለዋል። የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ መሳፍንት ተፈራ በበኩላቸው÷ ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን በዲጂታል ሚዲያ ዘርፍ እያስመዘገበ ያለውን ውጤት አድንቀው፣ በቀጣይም የበለጠ መስራት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል። ዘመናዊ የሆነው የዲጂታል ሚዲያ ዘርፍ በባህላዊ መንገድ ጥቅም ላይ ሲውል እንደነበር አንስተው÷ ዘመኑን መስሎ መጓዝ እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል።
ወሎ ዩኒቨርሲቲ በተለያዩ የምርምር ሥራዎች የህብረተሰቡን ችግር የሚያቃልሉ ተግባራት እያከናወነ ነው
Mar 18, 2025 111
ደሴ ፤ መጋቢት 9/2017(ኢዜአ) ፡- ወሎ ዩኒቨርሲቲ በተግባር ተኮር ትምህርት ብቁና ተወዳዳሪ ትውልድ ከማፍራት ባለፈ በተለያዩ የምርምር ሥራዎች የህብረተሰቡን ችግር የሚያቃልሉ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን አስታወቀ፡፡ የዩኒቨርሲቲ - ኢንዱስትሪ ትስስር መድረክ ዛሬ በደሴ ከተማ ተካሂዷል፡፡   በመድረኩ ላይ የወሎ ዩኒቨርሲቲ ምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት ሐዋ ወሌ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ተቋሙ ለተግባር ተኮር ትምህርት ትኩረት በመስጠት የትምህርት ጥራቱን ከማረጋገጥ ባለፈ በቴክኖሎጂ የበለጸገ ብቁና ተወዳዳሪ ትውልድ ለማፍራት በቅንጅት እየሰራ ይገኛል፡፡ ችግር ፈቺ ጥናትና ምርምር በማካሄድም የህብረተሰቡን ችግር በመፍታት ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ ወደ ተግባር የሚቀየሩ በርካታ ምርምሮች እየተሰሩ ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም በአካባቢው ከሚገኙ ኢንዱስትሪዎችና ምርምር ተቋማት ጋር ጭምር ትስስር በመፍጠር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችን በማበረታታት ሥራ ፈጣሪ ትውልድ ለማፍራት የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡   በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ የምርምርና የማህበረሰብ ጉድኝነት ጉዳዮች ተጠባባቂ መሪ ሥራ አስፈጻሚ ሠራዊት ሀንዲሶ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ከመማር ማስተማር ሥራቸው በተጓዳኝ የቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲያደርጉ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ከኢንዱስትሪዎች እና ከቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት ጋር በማስተሳሰር የማህበረሰቡን ችግር ማቃለል እንዲችሉ፣ ሁለንተናዊ ምርታማነትን እንዲያሳድጉ ሪፎርም ጭምር ተሰርቶ እየተተገበረ ይገኛል ብለዋል፡፡ ተማሪዎች በንድፈ ሀሳብ የሚማሩትን በተግባር በማሳየት በቂ እውቀትና ግንዛቤ እንዲኖራቸው ከዩኒቨርሲቲ ጋር ትስስር መፈጠሩን የተናገሩት ደግሞ በአማራ ክልል መንግስታዊ የልማት ድርጅት የሆነው የብረታብረት ኢንዱስትሪ ማሽን ቴክኖሎጂ ኮምቦልቻ ቅርንጫፍ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ ፋጡማ ይማም ናቸው፡፡   በዚህም የማሽኖችን ተግባርና አሰራር ተረድተው የቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲያደርጉ እየተደረገ ነው ፤ ከሥራ ጠባቂነት ሥራ ፈጣሪ መሆን እንዲችሉም ምቹ ሁኔታ እየተፈጠረ ነው ብለዋል፡፡ የኮምቦልቻ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ሥራ አስኪያጅ አቶ ሙሉጌታ መኮንን በበኩላቸው፤ ከዩኒቨርሲቲው፣ ከቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ጋር ትስስር በመፍጠር የቴክኖሎጅ እውቀት ሽግግር እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመድረኩ የዩኒቨርሲቲው፣ የዞን፣ የከተማ አስተዳደር፣ የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ኮሌጆች እንዲሁም በአካባቢው የሚገኙ ኢንዱስትሪዎች አመራር አባላትና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡    
ዩኒቨርሲቲው የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ምርምር እና ስልጠና ላይ አተኩሮ እየሰራ ነው
Mar 18, 2025 97
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2017(ኢዜአ)፦ ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በአቅም ግንባታ ስልጠና እና ምርምር ላይ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ አስታወቀ፡፡ ዩኒቨርሲቲው በክረምት መርኃ ግብር ብቻ ከ6 ሺ 500 ለሚልቁ መምህራን እና አመራሮች የአቅም ማጎልበቻ ስልጠና መስጠቱ ተመላክቷል፡፡ ለትምህርት ጥራት መጓደል የትምህርት ዩኒቨርሲቲ አለመኖር እንደ ምክንያት ሲነሳ የቆየ ሲሆን ይህንኑ ችግር ለመቅረፍ ዩኒቨርሲቲው በአዋጅ ተቋቁሞ ወደ ስራ ገብቷል፡፡ የኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ብርሃነመስቀል ጠና (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ተልዕኮ ወስዶ ወደ ስራ ከገባ አንስቶ አመርቂ ውጤት አስመዝግቧል፡፡ በዚህም የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት ባለፉት ጥቂት አመታት ውጤታማ ተግባራትን ማከናወኑን አስታውቀዋል፡፡ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የመምህራንን እና የአመራሮችን አቅም ማሳደግ ወሳኝ በመሆኑ የእቅም ግንባታ ላይ አተኩሮ እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በትምህርት ሚኒስቴር ስር መምህራንን የሚያሰለጥኑ ባለሙያዎችን በስፋት እያስተማረ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው ከክልል ትምህርት ቢሮዎች ጋር በመፈራረም የትምህርት ጥራትን የሚያረጋግጡ የምርምር ስራዎች እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። ለአብነትም ከአዲስ አበባ፣ ከኦሮሚያ እና ከአፋር ትምህርት ቢሮዎች ጋር በመፈራረም በርካታ የጥናትና የምርምር ስራዎች በመከናወን ላይ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው የጀመረው ስራ ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን ባለድርሻ አካላት ሚናቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ አሳስበዋል፡፡ የቀድሞው ኮተቤ ሜትሮፖሊታን ዩኒቨርሲቲ በ2014 ዓም ተጠሪነቱ ለትምህርት ሚኒስቴር ሆኖ በአዋጅ ወደ ኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ መቀየሩ ይታወሳል።
የፈጠራ አቅም ያላቸው ታዳጊዎች ለማፍራት አዳዲስ መርሐ ግብሮች ወደ ተግባር ገብተዋል
Mar 18, 2025 88
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2017(ኢዜአ)፦ ዕምቅ የፈጠራ አቅምና ችሎታ ያላቸው ታዳጊዎችን ለማፍራት አዳዲስ መርሐ ግብሮች ወደ ተግባር መግባታቸውን የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ገለፀ። ሚኒስቴሩ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር "ብሩህ እናት" የተሰኘ የሴት ኢኖቬተሮች የፈጠራ ሃሳብ ውድድር የቡት ካምፕ ስልጠና ማስጀመሪያ መርሃ ግብር እየተካሄደ ነው።   የስራና ክህሎት ሚንስትር ዴኤታ አቶ ሰለሞን ሶካ በወቅቱ እንዳሉት የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ ለማሳካት የቴክኖሎጂ ሽግግር ማድረግ አስፈላጊ ነው። ለዚህም የስራና ክህሎት ሚኒስቴር አዳዲስ ቴክኖሎጂ የሚያመነጩና የፈጠራ ሃሳብ ያላቸውን ወጣቶች የሚደግፉ መርሐ ግብሮችን እየቀረጸ መሆኑን ጠቅሰዋል። ይህንንም ተከትሎ አዳዲስ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ እምቅ አቅምና ችሎታ ያላቸውን ታዳጊዎችና ወጣቶች ለማፍራት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህም በተጨማሪ ችግር ፈቺ የፈጠራ ሃሳብ ያላቸው ዜጎች ሃሳባቸው ወደ ተግባር ተቀይሮ ተጨባጭ ውጤት እንዲያስገኝ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህ ረገድ አዳዲስ ቴክኖሎጂ የሚያመነጩና የፈጠራ ሃሳብ ያላቸውን ወጣቶች የሚደግፉ ፕሮግራሞች በመቅረፅ ተግባራዊ እየተደረጉ ነው ብለዋል፡፡ “ማሰልጠን፣ መሸለም እና ማብቃት” በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄደው “ብሩህ ኢትዮጵያ” ሀገር አቀፍ የቢዝነስ ፈጠራ ሃሳብ ውድድር ከእነዚህ ፕሮግራሞች መካከል አንዱ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በመርሐ ግብሩ በውድድር ያለፉ 50 የፈጠራ ሀሳብ ያላቸው ሴቶች ተጨማሪ ስልጠና እንደሚወስዱ ጠቅሰዋል። ከስልጠና በኋላ በውድድሩ ለሚያሸንፉ 10 ምርጦች ከመቶ ሺህ እስከ ግማሽ ሚሊዮን ብር ሽልማት እንደሚሰጣቸው ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም