ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
የቺካጎ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ስድስት ተቀራራቢ ፕላኔቶች ማግኘታቸውን ገለጹ
Nov 30, 2023 41
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ)፦ ስድስት ተቀራራቢ ፕላኔቶች ማግኘት መቻላቸውን በአሜሪካ የቺካጎ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች አስታወቁ። ተገኙ የተባሉት ፕላኔቶች በራሳቸው የጸሃይ ስርአት ዙሪያ የሚያደርጉት እንቅስቃሴ ስርአቱን የጠበቀና ሙዚቃዊ ስልት ያለው መሆኑንም ተመራማሪዎቹ ይፋ ባደረጉት ምስል ገልጸዋል። ኤች ዲ 110067 የሚል ስያሜ የተሰጣቸው ፕላኔቶቹ ኮማ ቤሬኒሲስ ከተባለው የህብረ ክዋክብት ስብስብ በአንድ መቶ የብርሃን አመታት ይርቃሉ መባሉን ኔቸር የተባለውን የምርምር መጽሄት ጠቅሶ ዩ ፒ አይ በድረ ገጹ አስነብቧል። የፕላኔቶቹ መገኘት ስለፕላኔቶች አፈጣጠር እና ዝግመተ ለውጥ አዲስ እይታ ሊፈጥር ይችላል የሚሉት የጥናት ቡድኑ መሪ ራፋኤል ሊዩክ “መሰል ግኝቶች ኔፕቱን በተባለችው ፕላኔት ዙሪያ ያሉ አካላት እንዲታወቁ እድል ይፈጥራል” ማለታቸውን ዘገባው አስታውሷል። “ምድር ካለችበት የጸሃይ ስርአት ውጪ ያሉ ሌሎች ፕላኔቶች አፈጣጠር፣ ቆይታ፣ የተሰሩበት ነገር ውሃ ስለመያዛቸው እና ሌሎች ጉዳዮች የጥናቱ መነሻ እንዲሆን አስችሏል” ብለዋል ተመራማሪው። የአሜሪካው ብሄራዊ የጠፈር ምርምር ኤጀንሲ ናሳ ከአውሮፓ የጠፈር ጥናት ድርጅት ጋር በመሆን በተላኩት ሳተላይቶች የክዋክብቱን የብርሃን መጠን፣ ከሌሎች ከዋክብት ጋር ያላቸውን መስተጋብር መመልከት እንደተቻለም ተገልጿል። እንደ ተመራማሪዎቹ ገለጻ ፕላኔቶቹ እርስ በእርስ ያላቸውን ርቀት የሚያስጠብቁበት ሬዞናንስ የተባለው ስርአት ያላቸው በመሆኑ በጸሃይ ዙሪያ ያሉት በርካታ ክዋክብት በሚያደርጉት መሽከርከር የሚጋጩባቸው አጋጣሚዎች በእጅጉ አናሳ መሆኑን በዘገባው ተመላክቷል።
የጂንካ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ችግር ፈቺና ፈርጀ ብዙ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለተጠቃሚዎች እያሻገረ ነው
Nov 29, 2023 189
ጂንካ፤ ህዳር 19/2016 (ኢዜአ)፡- የጂንካ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ውጤታማ፣ ችግር ፈቺና ፈርጀ ብዙ የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለተጠቃሚዎች ለማሻገር አትኩሮ እየሰራ መሆኑን ገለጸ ። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የኮሌጁ ዲን አቶ ካሳሁን ጌታቸው እንዳሉት፤ ኮሌጁ ችግር ፈቺ የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለማህበረሰቡ በማሸጋገር ተጠቃሚ ለማድረግ አልሞ እየሰራ ይገኛል። ኮሌጁ በአካባቢው የሚገኙ ያልተነኩ አቅሞችን ለመጠቀም የተጀመሩ ጥረቶችን ለማገዝ የማህበረሰቡን ድካም የሚቀንሱና ውጤታማነትን የሚያጎለብቱ ቴክኖሎጂዎች ማፍለቅና ማሸጋገር ላይ ዋናው ትኩረት አድርጎ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል ። በተለይ ኮሌጁ ''ኢትዮጵያ ታምርት'' በሚል መሪ ሀሳብ በተጀመረው አገራዊ ንቅናቄ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡ ማሽነሪዎችን በሀገር ውስጥ ምርቶች ለመተካት ባደረገው እንቅስቃሴ ውጤት እየተገኘ መሆኑን ጠቁመዋል። ለአብነት በኮሌጁ ከተሰሩ የፈጠራ ስራዎች መካከል ከ30 እስከ 40 ሜትር ጥልቅ ጉድጓድ መቆፈር የሚያስችል ማሽን መሰራቱን ያነሱት አቶ ካሳሁን ከውጭ ሲገባ ከሚጠይቀው ወጪ አንጻር እጅግ ዝቅተኛ በሆነ ዋጋ ለማህበረሰቡ እየቀረበ እንደሚገኝ ነው የተናገሩት። ኮሌጁ የአርሶ አደሮችን ድካም ለማቃለል ከፈጠራቸው ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎች መካከል የበቆሎ መፈልፈያ፣ የገብስና የጥራጥሬ መፈተጊያ ማሽኖች ይገኙበታል። የገብስና የጥራጥሬ መፈተጊያ ማሽኑም በባህላዊ መንገድ ጤፍ፣ ማሽላና ሌሎች ሰብሎችን በመውቃት የሚገጥመውን የምርት ብክነት መቀነስ የሚያስችል ቴክኖሎጂ መሆኑን አመላክተዋል። በኮሌጁ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን ባለሙያ አቶ እስጢፋኖስ እያሱ በኮሌጁ የፈለቁ ማሽኖች የኃይል አማራጭ ስላላቸው መብራት በሌለባቸው አካባቢዎች በነዳጅ የሚሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህም ከኃይል አቅርቦት ጋር የሚስተዋሉ ችግሮችን መቅረፍ የሚያስችል ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂ ነው ያሉት። ማሽኑ የኃይል አማራጭ እንዲኖረው መደረጉ አርሶ አደሮች እና በግብርና ላይ የተሰማሩ ኢንቬስተሮች ማሽኑን በተለያየ ቦታ በማንቀሳቀስ መጠቀም እንዲችሉ ታስቦ እንደተሰራም አስረድተዋል። በተለይ ተቋሙ የፈጠረው የጥራጥሬ መፈተጊያ ማሽን ስንዴ፣ ገብስ፣ ማሽላ እና ሩዝ መፈተግ የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰዋል። ይህም የአርሶ አደሩን ጊዜና ጉልበት ከመቆጠቡም ባሻገር የምርት ብክነትን ያስቀራል ብለዋል። በገጠር አካባቢዎች በስፋት የሸክላ ሥራ የሚተገበርና አሰራሩም ሁዋላ ቀር በመሆኑ ከዘርፉ የሚገኘው ኢኮኖሚያዊ ጥቅም አነስተኛ መሆኑን የገለፁት አቶ እስጢፋኖስ፤ ስራው በሰው ጉልበት በመሰራቱ እጅግ አድካሚ እንደሆነም አንስተዋል። ኮሌጁ ይህን ችግር በማየት የሸክላ አፈር መፍጨት፣ ማቡካትና የተለያዩ ቅርፆችን እንዲይዝ የሚያደርግ ዘመናዊ የሸክላ መስሪያ ማሽን መስራት ችሏል ብለዋል። ኮሌጁ የእርሻ ስራውን ለማዘመን እና የከብት እርባታውን አዋጭ ለማድረግ ከሚያግዙ ቴክኖሎጂዎች መካከል አነስተኛ የእርሻ ትራክተር እና የወተት መናጫ ማሽን እና ሌሎችንም ማፍለቅ መቻሉንም ገልጸዋል ። በፈጠራ ስራዎች ላይ ከተሳተፉ የኮሌጁ ተማሪዎች መካከል ተማሪ ሙሉቀን አለማየሁ ለኢዜአ እንደገለፀው በኮሌጁ 30 በመቶ የንድፈ ሃሳብ፣ 70 በመቶ የሚሆነውን ደግሞ በተግባር ልምምድ እንደተማሩ ተናግሯል። የጂንካ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በአሁኑ ወቅት በግብርና፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በኮንስትራክሽን እና በሌሎች ተዛማጅ የትምህርት መስኮች 501 ነባር ተማሪዎችን እያሰለጠነ ሲሆን ለ2016 ዓ.ም የትምህርት ዘመን ደግሞ 600 ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር በዝግጅት ላይ ይገኛል። ከመደበኛ የመማር ማስተማር ሰራው ጎን ለጎን 1 ሺህ ለሚሆኑ ሰልጣኞች በገበያ አዋጭነትና ስራ ፈጠራ ላይ አጫጭር ስልጠናዎችን ለመስጠት መዘጋጀቱንም ከኮሌጁ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የ5-ጂ ሞባይል ኔትዎርክ መስፋፋት የዲጂታል ልማትን ከማፋጠን ባለፈ ሀገራዊ የምጣኔ ኃብት እድገትን ለማረጋገጥ ሚናው የላቀ ነው
Nov 29, 2023 62
አዲስ አበባ ፤ህዳር 19/2016 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ የአምስተኛው ትውልድ (5-ጂ) የሞባይል ኔትዎርክ አገልግሎት መስፋፋት የዲጂታል ልማትን ከማፋጠን ባለፈ ሀገራዊ የምጣኔ ኃብት እድገትን ለማረጋገጥ ሚናው የላቀ መሆኑን የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ። ኢትዮ-ቴሌኮም የአምስተኛውን ትውልድ (5-ጂ) የሞባይል ኔትዎርክ በጅግጅጋ ከተማ በይፋ አስጀምሯል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ፤ በማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት በዓለም ላይ እጅግ ፈጣን የሚባለውን የአምስተኛው ትውልድ (5-ጂ) የሞባይል ኔትዎርክ ኢትዮጵያ መጠቀም ጀምራለች ብለዋል። የአምስተኛው ትውልድ (5-ጂ) ኔትዎርክ ተጠቃሚ ከሆኑ የዓለም አገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ መሆኗንም ጠቅሰዋል። የ5-ጂ ኔትዎርክ ቀደም ሲል በአዲስ አበባ እና አዳማ በይፋ መጀመሩን አስታውሰው፤ አሁን ላይ በሱማሌ ክልል ጅግጅጋ ከተማ በመጀመሩ እንኳን ደስ ያላችሁ ብለዋል። በኢትዮጵያ የማስፋፋት ሥራው በልዩ ትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይም ተጠናከሮ ይቀጥላል ሲሉ ተናግረዋል። የአምስተኛው ትውልድ (5-ጂ) የሞባይል ኔትዎርክ አገልግሎት የማስፋፋት ሥራ ለዲጂታል ኢትዮጵያ እውን መሆን የላቀ አስተዋጽዖ እንዳለውም ገልፀዋል። የ5-ጂ ኔትዎርክ አገልግሎት በጅግጅጋ ከተማ መጀመሩም የንግድና የመረጃ ሥርዓቱን ለማሳለጥና የመንግሥትን አገልግሎት አሰጣጥ የሚያቀላጥፍ መሆኑን ጠቅሰዋል። የሱማሌ ክልል ምክትል ርዕሰ-መስተዳድር ኢብራሂም ኡስማን፤ የቴክኖሎጂው እውን መሆን በክልሉ ለተጀመሩ የልማት ሥራዎች መፋጠን እንዲሁም በተለያዩ ሴክተሮች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያግዝ መሆኑን ገልፀዋል። በጅግጅጋ ኢዜአ ካነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ራሁ ጠይብካስ እና አብዱረዛቅ ሐሰን የአምስተኛው ትውልድ (5-ጂ) የሞባይል ኔትዎርክ አገልግሎት መጀመር በንግዱም ይሁን በሌሎች አገልግሎቶች ተጠቃሚ የሚያደርግ በመሆኑ ተደስተናል ብለዋል። የ5-ጂ የኔትዎርክ አገልግሎት በተለይም ለስማርት ሲቲ፣ ስማርት ትራንስፖርት፣ የትምህርት ሥርዓት፣ ለጤና፣ ለውሃ፣ የግብርና ልማት፣ ለንግድና የፋይናንስ ሴክተር፣ ለኢንዱስትሪ፣ ለስማርት የመንግሥት አስተዳደር እና ሌሎችም ሴክተሮች የላቀ አበርክቶ እንዳለው ይነገራል።
አብርሆት ቤተመጻሕፍት የቴክኖሎጂ እና የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ሰልጣኞችን ተቀበለ
Nov 28, 2023 71
አዲስ አበባ፤ ህዳር 18/2016 (ኢዜአ)፦ የአብርሆት ቤተመጻሕፍት አምስተኛ ዙር የቴክኖሎጂ እና የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ሰልጣኞችን ዛሬ ተቀብሏል። ለሰልጣኞቹም የቤተመጻሕፍቱ ዳይሬክተር ኢንጂነር ውብአየሁ ማሞ አቀባበል ያደረጉ ሲሆን የእንኳን ደህና መጣቹ መልእክትም አስተላልፈዋል። አብርሆት ቤተመጻሕፍት ቀደም ሲልም በአራት ዙሮች 500 ሰልጣኞችን የተቀበለ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን በአሁኑ ዙር የከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ጨምሮ መስፈርቱን ያሟሉ 200 ተማሪዎችን በመቀበል ለ4 ወራት የሚሰጠውን ስልጠና እንዲቀላቀሉ ተደርጓል። እነዚህ ተማሪዎች በቆይታቸው Data Structure ፣ Algorithm እንዲሁም የ Arteficial Intelligence ስልጠና እንደሚወስዱ ተገልጿል። ሰልጣኞቹ የተማሩትን የቴክኖሎጂ እውቀት በመጠቀምም ችግር ፈቺ አንዲሁም አለምአቀፋ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የሚያስችላቸው መሆኑን አብርሆት ቤተመጻሕፍት ለኢዜአ የላከው መረጃ ያመለክታል።
ኢትዮ-ቴሌኮም አምስተኛው ትውልድ (5ጂ) የኢንተርኔት ኔትወርክ አገልግሎት በጅግጅጋ ከተማ አስጀመረ
Nov 28, 2023 85
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 18/2016 (ኢዜአ) ፡- ኢትዮ-ቴሌኮም አምስተኛው ትውልድ (5ጂ) የኢንተርኔት ኔትወርክ አገልግሎት በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ከተማ አስጀምሯል። አገልግሎቱን የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ በይፋ አስጀምረውታል። በመርሃ ግብሩ የሶማሌ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ኢብራሒም ኡስማንን ጨምሮ ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል። አገልግሎቱ በአገሪቱ በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት አሰጣጥን ይበልጥ በማዘመን ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በእጅጉ ያግዛል ተብሏል። የ (5ጂ) የኔትወርክ አገልግሎት ወደ ሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎችም ተደራሽ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ አረጋግጠዋል። ኢትዮ-ቴሌኮም ከዚህ ቀደም የ (5ጂ) የኢንተርኔት ኔትወርክ በአዲስ አበባና በአዳማ ከተማ ማስጀመሩ ይታወሳል።
የታዳሽ ኃይል አማራጮችን በመጠቀም በሚቀጥሉት አራት ዓመታት 35 በመቶ የገጠሩን ህዝብ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዷል
Nov 27, 2023 80
ሆሳዕና ፤ ህዳር 17/2016 (ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አራት ዓመታት የታዳሽ ኃይል አማራጮችን በመጠቀም 35 በመቶ የገጠር ህዝብን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ገለጸ። ሚኒስቴሩ በአማራጭ ሀይል የኤሌክትሪክ ኃይል በማመንጨት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ያዘጋጀው ስልጠና ዛሬ በሆሳዕና ከተማ ተጀምሯል። በመድረኩ መክፈቻ ላይ በሚኒስቴሩ የገጠር ኢነርጂ ቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር የስራ ሂደት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ብርሃኑ ወልዱ እንዳሉት፤ የታዳሽ ኃይል አማራጭን በመጠቀም የገጠሩን የሀገሪቱ ክፍል የኤሌክትሪክ ሀይል ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው። በዚህም በሚቀጥሉት አራት ዓመታት 150 ማይክሮ ሀይድሮ ሶላሮች ተገንብተው ለአገልግሎት የሚበቁ ሲሆን ይህም 35 በመቶ የሚሆኑ የገጠር ነዋሪዎችን የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላል ብለዋል። በዚህም እንቅስቃሴ አነስተኛ የሰላር ግሪድ አማራጮችን ጭምር በየአካባቢው እንዲደርስ በማድረግ በተለያየ መንገድ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ ጥረት መጀመሩን ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደምም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች 10 የሶላር ሚኒ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶችን በመተግበር በገጠር የሚኖረውን ማህበረሰብ በመስኖ ልማት፣ በአግሮ ፕሮሰሲንግና በሌሎች ዘርፎች ተጠቃሚ ማድረጉን አስታውሰዋል። ከኤሌክትሪክ አገልግሎት በተጨማሪም ማህበረሰቡ በሌሎች ልማታዊና ተዛማጅ ዘርፎች ላይ ተሰማርቶ ተጠቃሚነቱን እንዲያሳደግ ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ትኩረት ሰጥቶ በመስራት ላይ መሆኑንም አስረድተዋል። ይህን ዕቅድ ከግብ ለማድረስ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አጋር አካላትን በማስተባበር ጠንካራ ስራ በመስራት ላይ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል በኦሮሚያ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ የኢነርጂ ባለሙያ አቶ ቢቂላ ታምሩ የታዳሽ ኃይል አማራጭን በማስፋት በክልሉ ገጠር አካባቢዎች ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። ለአብነትም በክልሉ ሰበታና ፈንታሌ አካባቢዎች የውሃና የፀሀይ ታዳሽ ኃይል አማራጮችን በመጠቀም ኃይል ለማመንጨት በተሰራው ስራ ማህበረሰቡን ከመብራት አገልግሎት በተጨማሪ በሌሎችም ዘርፎች ተጠቃሚ ለማድረግ መቻሉን አክለዋል። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በሀድያ ዞን ግቤ ወረዳ በሚገኘው የለመሬ ተፋሰስን በመጠቀም የማይክሮ ሀይድሮ ፓወር ፕሮጀክት ግንባታ የመስመር ዝርጋታ ስራ ብቻ እንደሚቀረው የተናገሩት ደግሞ በዞኑ ውሃና ኢነርጂ መምሪያ የኢነርጂ ዘርፍ አስተባባሪ አቶ ደለለኝ ጌሚሶ ናቸው። ፕሮጀክቱ ከ300 በላይ የአካባቢውን አባወራና እማዎራዎች የኤሌክትሪክና የአነስተኛ ኢንዱስትሪዎች አገልግሎቶች ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። ለ10 ቀናት በሚሰጠው ስልጠና ላይ ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ የዘርፉ ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው።
ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን እና የአየር ንብረት ለውጥን ያማከሉ ፖሊሲዎች የአፍሪካን ኢኮኖሚ በፍጥነት ለማሳደግ ቁልፍ መንገዶች ናቸው
Nov 27, 2023 90
አዲስ አበባ፤ ህዳር 17/2016(ኢዜአ)፡- የዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን እና የአየር ንብረት ለውጥን ማእከል ያደረጉ የኢንዱስትሪ ፖሊሲዎች የአፍሪካን ምጣኔ ሃብት በፍጥነት ለማሳደግ ቁልፍ መንገዶች መሆናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ20ኛው የተባበሩት መንግሥታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ ንግግር አድርገዋል፡፡ ታሪክ እንደሚያሳየን ኢንዱስትራላይዜሽን በመቶ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ህዝቦች ከድህነት እንዲወጡ አስችሏል ብለዋል። በተለይም የማኑፋክቸሪንግ ሴክተር ሰፊ የስራ ዕድልን በመፍጠር እና የቴክኖሎጂ አቅምን በማሳደግ የሀገራት ብልጽግና ማረጋገጫ ቁልፍ መንገድ ሆኗል ነው ያሉት። ባለፉት ሁለት አስርት አመታት የኢንዱስትሪው አለም በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና በአየር ንብረት ለውጥ የተነሳ ቀድሞ ከነበረበት አካሄድ አብዮታዊ ለውጥ ማሳየቱን ተናግረዋል። የዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን እና የአየር ንብረት ለውጥን ማእከል ያደረጉ የኢንዱስትሪ ፖሊሲዎች የአፍሪካን ምጣኔ ሃብት በፍጥነት ለማሳደግ ቁልፍ መንገዶች ናቸው ሲሉ ጠቅሰዋል። በዚህ ረገድ የአፍሪካ ሀገራትም ከተቀረው የአለም ክፍል ጋር አካታችና ሁሉን አቀፍ የኢንዱስትሪ ልማትን ለማሳካት ዝግጁ ናቸው ብለዋል። አፍሪካ ያላትን ሰፊ አምራች የሰው ሃይል ጨምሮ እጅግ ተፈላጊ የሆኑ ማእድናትን ጨምሮ በተፈጥሮ ሀብት የታደለች አህጉር መሆኗንም አንስተዋል። ይህም ለላቀ የኢንዱስትሪ አምራችነትና ኢኮኖሚን ለማሳደግ አስፈላጊ ጉዳይ መሆኑን አስረድተው መንግስታት ለአካታችና ሁሉን አቀፍ ብልጽግና በጋራ መስራት ይኖርብናል ብለዋል።
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር እና የስራና ክህሎት ሚኒስቴር በጋራ ለመስራት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ
Nov 27, 2023 72
አዲስ አበባ፤ ህዳር 17/2016 (ኢዜአ)፦ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር እና የስራና ክህሎት ሚኒስቴር በቴክኖሎጂና የስራ እድል ፈጠራ በጋራ ለመስራት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ። የመግባቢያ ስምምነቱ ሁለቱ ተቋማት በተለይም በ'ግድቤ በደጄ' የውሃ ፕሮጀክት ለወጣቶች የስራ ዕድል ለመፍጠር እና ቴክኖሎጂውን ለማስፋፋት የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጅነር ሃብታሙ ኢታፋ እና የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ስምምነቱን ተፈራርመዋል። በስምምነቱ መሰረት በ'ግድቤን በደጄ' ፕሮጀክት የዝናብ ውሃን በማቆር ውሃን ለመጠቀም የሚያስችል ቴክኖሎጂን በመጠቀም ለመስኖ እና ውሃውን በማጣራት ለመጠጥ ማዋል የሚቻል ይሆናል። በመጀመሪያ ዙር በ11 ትምህርት ቤቶች በፓይለት ደረጃ የተተገበረ ሲሆን በሁለኛው ዙር በ87 ትምህርት ቤቶች ለማስፋፋት እየተሰራ ይገኛል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጅነር ሀብታሙ ኢታፋ፤ የፕሮጀክቱ መተግበር በሀገሪቷ ያለውን የውሃ ሃብት በአግባቡ ለመጠቀም የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። በፕሮጀክቱ የዝናብ ውሃን በቴክኖሎጂ በመታገዘ መልኩ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚሰራ መሆኑን ጠቅሰው የአገሪቱን የውሃ ሽፋን ለመጨመር ያግዛል ብለዋል። በትምህርት ቤቶች የተጀመረው ይህ ፕሮጀክት በቀጣይ በሁሉም አገሪቱ አካባቢዎች ለማስፋት የሚሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል፤ በውሃ ቴክኖሎጂ ላይ ብቁ እና የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራትና የቴክኖሎጂ ሽግግር ለማምጣት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ፕሮጀክቱ ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል ከመፍጠር የውሃ ሃብትን የሚያሳድግ በመሆኑ በስምምነቱ መሰረት የሚሰራ መሆኑን ሚኒስትሯ አረጋግጠዋል።
በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት አራት የትምህርት መርሃ ግብሮች ዓለም አቀፍ የጥራት ተቀባይነት አገኙ
Nov 26, 2023 90
አዲስ አበባ፤ ህዳር 16/2016 (ኢዜአ)፦በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ስር የሚገኙ አራት የትምህርት መርሃ ግብሮች ዓለም አቀፍ የጥራት ተቀባይነት አገኙ። በዚሁ ጉዳይ ላይ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዶክተር ፍሬው ተገኝ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም ዩኒቨርሲቲው ባለፋት 60 አመታት ዕውቅ ምሁራን ከማፍራት በተጨማሪ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለመሆን መስራቱንና አሁንም እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በዩኒቨርሲቲው ቴክኖለጂ ኢንስቲቲዩት ስር የሚገኙ አራት የትምህርት ዘርፎች በዓለም አቀፍ ደረጃ የጥራት ተቀባይነት ማግኘት መቻላቸውን ገልጸዋል። የኤሌክትሪካል፣ መካኒካል፣ የሲቪልና ኬሚካል ኢንጂነሪንግ ትምህርት ክፍሎችም እውቅናው የተሰጣቸው መሆኑን ጠቅሰዋል። ዕውቅናው ABET በተባለ አለም አቀፍ ድርጅት መሰጠቱን በመጥቀስ ይህም አለም አቀፍ መምህራንና ተማሪዎች ለመቀበል እድል ይፈጥራል ብለዋል። የተገኘው ዕውቅና በኢኒስቲቲዩቱ የሚሰጡ ስልጠናዎች በአለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት እንዲኖራቸው ያግዛል ብለዋል። ዩኒቨርሲቲው ዕውቅናውን ለማግኘት ላለፋት አራት አመታት ሰፋፊ ስራዎች ሲያከናውን መቆየቱንም አስረድተዋል። ዩኒቨርሲቲው ሐምሌ 15 ቀን 2015 ዓ.ም ባደረገው የተማሪዎች ምረቃ ሥነሥርዓት ላይ ለጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ የክብር ዶክትሬት ሽልማት መስጠቱም ይታወሳል። በዚሁ መሰረትም በዛሬው እለት በአዲስ አበባ በተከናወነ ስነ ስርአት ላይ ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ ከዩኒቨርሲቲው የተሰጣትን የክብር ዶክትሬት ተረክባለች።
የተቋማትን ምርትና አገልግሎት ዘመናዊና ቀልጣፋ በማድረግ ከተወዳዳሪነት ባለፈ ለሀገር እድገት እንዲሰሩ ማድረግ ይገባል- ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ
Nov 26, 2023 77
አዲስ አበባ፤ ህዳር 16/2016 (ኢዜአ)፦ የተቋማትን ምርትና አገልግሎት ዘመናዊና ቀልጣፋ በማድረግ ከተወዳዳሪነት ባለፈ ለሀገር እድገት እንዲሰሩ ማድረግ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ ገለጹ። የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት ያዘጋጀው 10ኛው ዙር አገር አቀፍ የጥራት ሽልማት ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በተገኙበት በትላንትናው እለት ተካሂዷል። የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት የሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ፤ በጥራት ውድድሩ ከሽልማት ባለፈ ተቋማት የተሞከሮ ልውውጥ እንዲያደረጉ የሚያግዝ ነው ብለዋል። በመሆኑም ተቋማት ምርትና አገልግሎታቸውን ቀልጣፋና ዘመናዊ በማድረግ ከሀገር አልፎ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለመሆን መስራት ይጠበቅባቸዋል ነው ያሉት። በቀጣይም ተቋማት የምርትና አገልግሎት ጥራትን በማረጋገጥ ለአገሪቱ እድገት የበኩላቸውን ሚና እንዲወጡ አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት ዋና ስራ አስፈጻሚ ቴዎድሮስ መብራት፤ በአምራች፣ በአገልግሎት፣ በጤና እና በትምህርት ዘርፍ የተሰማሩ ተቋማት በውድድሩ መሳተፋቸውን ገልጸዋል። በተቀመጠው እስታንዳርድ መሰረትም 38 ተቋማት በየደረጃው ሽልማት መውሰዳቸውን ጠቅሰው በቀጣይም አሰራራቸውን ይበልጥ በማዘመን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለመሆን እንዲሰሩ አስገንዝበዋል። ከተሸላሚዎቹ መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው የተቋማት ተወካዮች በተሰጣቸው እውቅና መደሰታቸውን ገልጸው በቀጣይ ለተሻለ ምርትና አገልግሎት መዘጋጀታቸውን አረጋግጠዋል።
ኢንስቲትዩቱ በምርምር ያገኛቸውን ዝርያዎች በራሱና በአርሶ አደሩ ማሳ በማባዛት ተደራሽ እያደረገ ነው
Nov 25, 2023 85
ሮቤ፤ ህዳር 15/2016 (ኢዜአ) ፦ የኦሮሚያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የምርምር ውጤቶችን ከማፍለቅ ባለፈ፤ በምርምር የተገኙ ዝርያዎችን በራሱና በአርሶ አደሩ ማሳ በማባዛት ተደራሽ እያደረገ መሆኑን አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ በሥሩ ባደራጃቸው የምርምር ማዕከላት የሚያደርጋቸው ምርምሮች በምግብ ራስን ለመቻል የሚደረገውን ጥረት ከማሳካት በተጓዳኝ የውጭ ምንዛሬ ማስገኘትን ታሳቢ ያደረጉ መሆኑም ተመላክቷል። የኦሮሚያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ተሾመ ቦጋለ እንደገለጹት፤ ኢንስቲትዩቱ የምርምር ውጤቶችን ከማፍለቅ ባለፈ በምርምር የተገኙ ዝርያዎችን በራሱና በአርሶ አደሩ ማሳ በማባዛት ተደራሽ እያደረገ ነው። ኢንስቲትዩቱ በሥሩ በሚገኙ 17 ማዕከላት አዳዲስ አሰራሮችንና ቴክኖሎጂዎችን በምርምር በማውጣትና በማላመድ አርሶ አደሩ እንዲጠቀምባቸው በማገዝ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን እየሰራ ነው ብለዋል። አቶ ተሾመ እንዳሉት፣ማዕከላቱ ባለፈው ዓመት ብቻ በሰብል ልማት፣በጥራጥሬና በእንስሳት መኖ ላይ ትኩረት ያደረጉ 19 ቴክኖሎጂዎችን በምርምር በማውጣት ለተጠቃሚዎች ማድረሱን ገልጸዋል። በምርምር የወጡ የተሻሻሉ ዝርያዎችን በስፋት ወደ አርሶ አደሩ እንዲደርሱ በኢንስቲትዩቱ ማዕከላት፣ በኢንተርፕራይዞችና በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በስፋት እንዲባዙ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ነው የተናገሩት። የሲናና ምርምር ማዕከል በሁለቱ የባሌ ዞኖች ውስጥ ለሚገኙ ሞዴል አርሶ አደሮች ከ80 ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ያከናወነው የዘር ብዜትም የዚሁ ጥረት ማሳያ ነው ብለዋል። እየተባዙ የሚገኙ የምርምር ዝርያዎች በምግብ ራስን ለመቻል የሚደረገውን ጥረት ለማሳካት ከማገዛቸውም በላይ፣የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት እንደሚያስችሉ አቶ ተሾመ አስረድተዋል። ከማዕከላቱ ያገኙትን የምርምር ውጤቶችን ተቀብለው ከሚያባዙ ተቋማት መካከል የኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ የባሌ ቅርንጫፍ አንዱ ነው። የቅርንጫፉ ተተኪ ዳይሬክተር አቶ ሙሉቀን አስቻለው እንዳሉት፤ ኢንተርፕራይዙ ከሲናና ግብርና ምርምር ማዕከልና ከሌሎች የግብርና ማዕከላት የሚያገኛቸውን ዝርያዎች ከ17 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ እያባዛ መሆኑን አስታውቀዋል። የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል ኃላፊ አቶ ታመነ ሚደቅሳ በበኩላቸው ማዕከሉ ከ1978 ዓ.ም ጀምሮ ከ97 የሚበልጡ የተለያዩ የሰብል ዝርያዎችና የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ለተጠቃሚዎች ማድረሱን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም ባለፈው ዓመት በምርምር ያገኘውን " ቦኩ" የሚል ስያሜ የተሰጠውና በሄክታር 72 ኩንታል ምርት የሚሰጥ የስንዴ ምርጥ ዘር በራሱና 80 ሄክታር በሚበልጥ የአርሶ አደሩ ማሳ ላይ እያባዛ መሆኑን ተናግረዋል። የአጋርፋ ወረዳው አርሶ አደር አቶ በየነ ታደሰ በሰጡት አስተያየት ከአምስት ዓመታት በፊት ምርጥ ዘርና የተሻሻሉ የግብርና አሰራሮችን እምብዛም ተግባራዊ ሳያደርጉ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። በዚህም በስንዴ ከሄክታር ከ15 ኩንታል የዘለለ ምርት አግኝተው እንደማያውቁ ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት የመኽር ወቅት ማዕከሉ ያገኙትን "ሳነቴ" የሚባል የስንዴ ዝርያ በማምረት ግን በሄክታር 60 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። በመኸር ወቅት በመሥመር የመዝራት ቴክኖሎጂን ጨምሮ የተሻሻሉ የግብርና አሰራሮችን በመጠቀም ከማዕከሉ ያገኙትን 'ቦኩ" የሚባል የስንዴ ዝርያ በአንድ ሄክታር ላይ አልምተው እየተንከባከቡ መሆኑን ገልፀዋል። አርሶ አደር በቀለ አሰፋ በበኩላቸው ከዚህ በፊት ሰብልን በወቅቱ በማረምና የአረም መከላከያ መድኃኒትን በመርጨት ረገድ ክፍተት ስለነበረ የልፋታቸውን ያህል ምርት ሳያገኙ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት የማዕከሉ ተመራማሪዎች በሚሰጧቸው ምክር በመታገዝ ማሳቸውን በማረምና በወቅቱ የአረም መከላከያ መድኃኒት በመርጨት በሄክታር እስከ 70 ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። የኦሮሚያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት በአሁኑ ወቅት ከ1ሺህ 400 በሚበልጡ መስኮች ላይ ምርምሮችን እያካሄደ መሆኑን ከኢንስቲትዩቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በሰው ሰራሽ አስተውሎት ምርታማነትን መጨመር የሚያስችል አቅም እየተፈጠረ ነው
Nov 24, 2023 97
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 14/2016 (ኢዜአ) ፦ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ፈጣንና ዘመናዊ አገልግሎት በመስጠት ምርታማነትን መጨመር የሚያስችል አቅም እየተፈጠረ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ገለጸ፡፡ ውጤታማነታቸው በሙከራ የተረጋገጠ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የምርምር ውጤቶች በቅርቡ ይፋ ሆነው ሥራ ላይ ይውላሉም ብሏል፡፡ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዳታን መሰረት በማድረግ የሰው ልጆችን ዕውቀት፣ ክህሎት፣ ቋንቋና እሳቤ በላቀ አረዳድና ግንዛቤ ተክቶ ለችግሮች መፍትሔ መስጠት የሚያስችል ቴክኖሎጂ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሁለንተናዊ አገልግሎት በዓለም ላይ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገና እየዘመነ መጥቷል። በኢትዮጵያም በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ሀሳብ አመንጪነት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በ2012 ዓ.ም ተቋቁሞ መስከረም 10 ቀን 2013 ዓ.ም ተመርቆ ስራ መጀመሩ ይታወሳል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ወርቁ ጋቸና ለኢዜአ እንዳሉት፤ ለግብርና፣ ለትምህርት፣ ለጤና እንዲሁም ለኅብረተሰብ ጥበቃና ደኅንነት የሚውሉ የምርምር ውጤቶች እየመጡ ነው፡፡ በኢንስቲትዩቱ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዳታ ማዕከል ተገንብቶ ለመንግስትና ለግሉ ዘርፍ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የጤናውን ዘርፍ ባለሙያዎች የሚያግዙ የምርምር ውጤቶችን ማፍለቅ እንዲሁም ማሽንን አገርኛ ቋንቋዎች በማስተማር የተለያዩ ስራዎችን ማከናወን ተችሏልም ብለዋል፡፡ በትራንስፖርት ዘርፉ "የኤሌክትሮኒክ ካርጎ ትራኪንግ ሲስተም" የተባለ የምርምር ሥራ በቅርቡ አገልግሎት ላይ እንደሚውልም ገልጸዋል፡፡ የወንጀል መከላከል ዘርፍን የሚያግዙ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የምርምር ውጤቶች በቅርቡ ይፋ እንደሚደረጉም ገልጸዋል፡፡ የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ታዬ ግርማ በበኩላቸው በዘርፉ የሰለጠኑ ባለሙያዎችን ለማፍራት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ አምስት አገርኛ ቋንቋዎች ለሰው ሰራሽ አስተውሎት ሥራ ላይ መዋላቸውን ጠቅሰው፤ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ሁሉንም ቋንቋዎች ተደራሽ እናደርጋለን ብለዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዘመናዊና ቀልጣፋ አሠራር ለመዘርጋት የተጀመሩ ጥረቶችን ያግዛል- ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ
Nov 23, 2023 95
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 13/2016 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በተለያዩ ዘርፎች ዘመናዊና ቀልጣፋ አሠራር ለመዘርጋት የተጀመሩ ጥረቶችን የሚያግዝ መሆኑን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማኔጅመንት አባላትና ሠራተኞች የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትን የሥራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል፡፡ በጉብኝቱ በሰው ሠራሽ አስተውሎት አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን፣ የጤና አገልግሎትን ለማሳለጥና የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎችን አድንቀዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ በዚሁ ወቅት፤ ኢንስቲትዩቱ ሀገር ከዘርፉ የምትፈልገውን አበርክቶ ለማሳካት በትክክለኛው መንገድ ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡ በመሆኑም የኢንስቲትዩቱን ሥራዎች በተለያየ መልኩ ከማገዝና መደገፍ ባለፈ በሰው ኃብት ልማት የድርሻችንን ለመወጣት እንሰራለን ብለዋል። በዘርፉ የግብርና፣ ቱሪዝም፣ ጤና እና የዲጂታል ኢኮኖሚ ዘርፍ ዘመናዊና ቀልጣፋ አሠራር ለመዘርጋት የተጀመረው ጥረት የሚደነቅ ነው ብለዋል። በመሆኑም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዘመናዊና ቀልጣፋ አሠራር ለመዘርጋት የተጀመሩ ጥረቶችን ያግዛል ሲሉ አረጋግጠዋል። በተለያዩ ዘርፎች ዘመናዊና ውጤታማ ተግባራትን ለማከናወን የተጀመሩ ጥረቶችን ዩኒቨርሲቲው እገዛና ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተቋማዊ ለውጥ ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ወንድወሰን ሙሉጌታ፤ በተቋሙ እየተከናወኑ ያሉ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ተግባራትን አድንቀዋል። በጉብኝታቸው የተመለከቱት የዳታ ማዕከልም ከሁሉም ተቋማት ለሚሰበሰቡ መረጃዎች እንደ ቋት የሚያገለግል ትልቅ የሀገር ኃብት መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና፤ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በርካታ አገራዊ ፕሮጀክቶችን በጋራ እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ በሁሉም የትምህርት ክፍል ያሉ የዩኒቨርሲቲው ምሁራን ለኢንስቲትዩቱ የበኩላቸውን በማበርከት ላይ በመሆናቸው አመስግነው፤ ይህንኑም አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በ2012 ዓ.ም ተቋቁሞ መስከረም 10 ቀን 2013 ዓ.ም ደግሞ መርቀው ሥራ ማስጀመራቸው ይታወሳል።
የአፍሪካን ዲጂታላይዜሽን በማፋጠን ሂደት የሁሉም አካላት ርብርብና ጥረት ሊታከልበት ይገባል- የአፍሪካ ሕብረት
Nov 23, 2023 92
አዲስ አበባ፤ ህዳር 13/2016(ኤዜአ)፦ የአፍሪካን ዲጂታላይዜሽን በማፋጠን ሂደት የሁሉም አካላት ርብርብና ጥረት ሊታከልበት እንደሚገባ የአፍሪካ ሕብረት ገለጸ። አፍሪካ ሕብረት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ቴክኒካል ኮሚቴ አምስተኛ መደበኛ ጉባዔውን አካሂዷል። አፍሪካ ሕብረት የመሠረተ-ልማትና ኢነርጂ ኮሚሽነር ዶክተር አማኒ አቡ-ዘይድ፤ በመድረኩ ባስተላለፉት መልዕክት የአፍሪካን ዲጂታላይዜሽን የማፋጠን ሂደት የሁሉንም ርብርብ ይፈልጋል ብለዋል። የአፍሪካ ሕብረት ይህንን ውጥን እውን ለማድረግ የተለያዩ ስትራቴጂዎችን ገቢራዊ እያደረገ መሆኑን ገልጸው፤ አባል አገራቱም ተመሳሳይ ስትራቴጂዎችን ገቢራዊ እያደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል። በአፍሪካ ኢኮኖሚያዊ እድገትን ለማፋጠን የሚከናወኑ የዲጂታላይዜሽን ሥራዎች ለማፋጠን እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይበልጥ ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ብለዋል። የአህጉሪቱን ዲጂታል ምህዳር ለማስፋት አገራት የፖሊሲ ስትራቴጂ እንዲያዘጋጁና እርስ በርስ እንዲያጣጥሙ በማድረግ ለውጦች እየታዩ መሆኑን ጠቅሰዋል። ጎን ለጎንም የሳይበር ደኅንነትንና የግል መረጃን ለመጠበቅ የተደረሰው ስምምነት መፅደቁን ጠቁመው፤ ይህም ካለፈው ሰኔ ጀምሮ ገቢራዊ መሆን መጀመሩን ጠቁመዋል። የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ልማትን ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት መሥራት ያስፈልጋልም ነው ያሉት። የአፍሪካ ሕብረት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2030 በኢኮኖሚ ልማት፣ የማኅበረሰብ ለውጥና ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ ለያዘው ዕቅድ ስኬት የአባል አገራት ሁለንተናዊ ጥረትና በተለይም የዲጂታል ልማት ግንባታ ልዩ ትኩረት የተሰጠው መሆኑ ይታወቃል።
ኢንስቲቲዩቱ "የአፍሪካ የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የልሕቀት ማዕከል” እንዲሆን የቀረበውን ሃሳብ የጋራ ኮሚቴው ተቀበለው
Nov 23, 2023 81
አዲስ አበባ፤ ህዳር 13/2016(ኤዜአ)፦ የኢትዮጵያ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት "የአፍሪካ የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የልሕቀት ማዕከል” እንዲሆን የጋራ የቴክኒክ ኮሚቴው ያቀረበውን ምክረሃሳብ የሚንስትሮች ምክርቤት የጋራ ኮሚቴ ተቀበለው። የአፍሪካ የአይሲቲ እና ኮሚኒኬሽን ሚንስትሮች መደበኛ ጉባኤ በህብረቱ የስብሰባ አዳራሽ እየተካሄደ ነው። በጉባኤው ኢትዮጵያን በመወከል የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚንስቴር የኤሌክትሮኒክ መንግስት ልማት መሪ ሥራ አስፈፃሚ ዶ/ር ኢንጂነር አብዮት ሲናሞ እየተሳተፉ ይገኛሉ። በስብሰባው የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት “የአፍሪካ የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ የልሕቀት ማዕከል” እንዲሆን በኢትዮጵያ በኩል ጥያቄው ቀርቦ በአፍሪካ አገራት የአይሲቲና የኮሙኒኬሽን ሚኒስቴሪያል አባላት ቀርቦ ውሳኔ እንዲሰጥበት በጋራ ኮሚቴው ተቀባይነት አግኝቷል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን በኮሚኒኬሽን እና በአይሲቲ ላይ የሚመክረው የልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ 5ኛ መደበኛ ስብሰባ ከህዳር 10 እስከ 12 ቀን 2016 በአፍሪካ ሕብረት አዳራሽ ለሦስት ቀናት መካሄዱ እና ውሳኔዎች እንደቀረቡበት ከኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
የኢትዮጵያ ከተሞችን ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት አሰጣጥ ወደ ዲጂታል የማሸጋገር ስራ እየተሰራ ነው - ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ
Nov 22, 2023 106
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 12/2016 (ኢዜአ) ፦የኢትዮጵያ ከተሞችን ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት አሰጣጥ ወደ ዲጂታል የማሸጋገር ስራ እየተከናወነ መሆኑን የከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ፡፡ የመንግሥት የ2016 የመጀመሪያ ሩብ በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ተጀምሯል። በግምግማው የከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር የስራ እንቅስቃሴዎች ተዳሰዋል፡፡ የከተማ እና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ እንደገለጹት፤ በመጀመሪያው ሩብ ዓመት የማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶችን ለማዘመን በርካታ ስራዎች ተሰርተዋል፡፡ በስድስት ከተሞች የአገልግሎት ደረጃዎችን በማዘጋጀት ተግባራዊ እንዲያደርጉ ዕቅድ ተይዞ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ከተሞቹ በቄራ አገልግሎት፣ በአረንጓዴ ልማትና የከተማ ውበት፣ በቆሻሻ አወጋገድ፣ በግንባታ ፈቃድ አሰጣጥ እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች አገልግሎታቸውን እንዲያዘምኑ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የከተሞች አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን እና ከሰው ንክኪ ነጻ ወደ ሆነ ዲጂታላይዜሽን ለማሸጋገርም ለአብነት በቀብሪደሃር፣ ጅግጅጋ፣ በደብረብርሃን እና ቢሾፍቱ ከተሞች ላይ እየተሰራ ነው ብለዋል። በእነዚህ ከተሞች የሚገኘውን ተሞክሮ ወደ ሌሎች ለማስፋት ዕቅድ መያዙንም ጠቅሰዋል። የከተሞች የመሬት አያያዝ ስርዓትን ለማዘመን በካዳስተር ስርዓት መመዝገብ መጀመሩን ያነሱት ሚኒስትሯ፤ ይህም የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠት እና ብልሹ አሰራሮችን ለመቅርፍ ያስችላል ብለዋል፡፡ በሩብ ዓመቱ ከከተሞች የማዘጋጃ ቤት አገልግሎት 6 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን ጠቅሰዋል። የከተሞች የገቢ አቅም ማደጉ ምቹ ከባቢን ለመፍጠር፣ ኢንቨስተሮችን ለመሳብ እና መሰረተ ልማቶችን በራስ አቅም ለመገንባት ትልቅ ፋይዳ እንዳለውም ነው የተናገሩት።
ኢትዮ-ቴሌኮም አዳዲስ የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነትን ለማስፋት እየሰራ ነው
Nov 17, 2023 145
አዲስ አበባ፤ ህዳር 7/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮ-ቴሌኮም የፋይናንስ አካታችነትንና አዳዲስ የዲጂታል አገልግሎቶችን ለማስፋት የሚያከናውናቸውን ተግባራት አጠናክሮ እንደሚቀጥል የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ገለፁ። ኢትዮ-ቴሌኮም የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለትን አስተዳደር ሥርዓት፣ የነዳጅ ኩፖንና የሦስተኛ ወገን ኢንሹራንስ ዲጂታል ለማድረግ የሚያስችል አሠራር ዛሬ ይፋ አድርጓል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ በዚሁ ጊዜ እንደገለፁት፤ ነዳጅን የተመለከቱ የዲጂታል ሥርዓቶች የነዳጅ ኩባንያዎች የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን ያስችላል። ይህም ግልጽነት ለመፍጠርና ትክክለኛ መረጃዎች በወቅቱ ለማግኘት የሚያስችል ነው ተብሏል። ይህም ብቻ ሳይሆን የነዳጅ ማደያዎችን የአገልግሎት አማራጭ ለማሳደግ፣ ግብይቶችን ለማሳለጥ እንዲሁም የገንዘብ ፍሰትን ለማሻሻል ትልቅ አበርክቶ እንዳለው ነው ያስረዱት። የሦስተኛ ወገን የመድን አገልግሎት በዲጂታል ለመስጠት የሚያስችለው ሥርዓትም በትክክለኛ መረጃ ላይ መሠረት ያደረገ የተማከለ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ብለዋል። ኩባንያው የተለያዩ ዘመናዊ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በማስተዋወቅ የአገሪቱን ምጣኔ ኃብታዊ እድገት ለማስቀጠል የሚያከናውናቸውን ተግባራት አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል። የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሳህረላ አብዱላሂ በበኩላቸው፤ የዲጂታል አሠራሮቹ ዘመናዊ የነዳጅ ግብይት ለማጠናከር ያግዛል ብለዋል። በተለይም የዲጂታል ኩፖን መረጃዎችን ለመቆጣጠር እንዲሁም ደኅንነቱ የተጠበቀ ግብይት ለማካሄድ ያስችላል ሲሉም ነው ዋና ዳይሬክተሯ የተናገሩት። የኢትዮጵያ መንገድ ደኅንነትና መድኅን ፈንድ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጀማል አባሶ፤ የሦስተኛ ወገን ኢንሹራንስ ዲጂታል መሆን በርካታ ጠቀሜታ አለው ብለዋል። ይህም በኢንሹራንስ ሂደቶች ውስጥ የሚከሰቱትን ተግዳሮቶች ለመቀነስ ያግዛል ነው ያሉት።
ኢትዮ-ቴሌኮም የትራንስፖርት እና የነዳጅ አቅርቦትን የሚያዘምን ሥርዓት ይፋ አደረገ
Nov 17, 2023 135
አዲስ አበባ፤ ህዳር 7/2016 (ኢዜአ)፦ ኢትዮ-ቴሌኮም የትራንስፖርት እና የነዳጅ አቅርቦትን የሚያዘምን የቴክኖሎጂ ስርዓት ይፋ አደረገ። ዛሬ ይፋ የሆነው ስርዓት ዲጂታል የነዳጅ መሙያ ኩፖን፣ ዲጂታል የሶስተኛ ወገን መድህን እና ዲጂታል የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለት ያካተተ ሲሆን፤ በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን ይቀርፋል ተብሏል። ለአብነትም የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለትን በተማከለ የዲጂታል ሥርዓት ለማሳለጥ እንደሚያስችል ተገልጿል። በወረቀትና በሰው ንክኪ የሚፈጸም የነዳጅ ኩፖን ሽያጭ አገልግሎት አሰራርን በዲጂታል ኩፖን በመቀየር እመርታዊ ለውጥ እንደሚያመጣም ተጠቁሟል። በሌላ በኩል የሶስተኛ ወገን መድህን አገልግሎትን በዲጂታል ለመስጠት እንደሚያስችል ነው የተነገረው። በመርኃ ግብሩ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ፣ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን፣ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ ደገፉ፣ የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሳህረላ አብዱላሂ፣ የመንገድ ደህንነት እና መድህን ፈንድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጀማል አባስ እና የነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ እስመለዓለም ምህረቱ ተገኝተዋል።
በሲዳማ ክልል በተመረጡ የመንግስት ተቋማት የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት ሊተገበር ነው
Nov 13, 2023 196
ሀዋሳ፤ ህዳር 3 / 2016 (ኢዜአ) ፡- በሲዳማ ክልል በተመረጡ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት ለመተግበር ዝግጅት ማጠናቀቁን የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው ዘመናዊና ቀልጣፋ የፋይናንስ አሰራር ለመዘርጋት የሚያስችል የውል ስምምነት ዛሬ ከአንድ ድርጅት ጋር ተፈራርሟል። በስነ ስርዓቱ ላይ የቢሮው ኃላፊ ዶክተር አራርሶ ገረመው እንዳሉት ፤ በክልሉ በተመረጡ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት ይተገበራል። በዚህም በክልሉ ከሚገኙ የመንግስት መስሪያ ቤቶች መካከል በድህነት ቅነሳ መርሃ ግብር አተኩረው በሚሰሩ ስድስት ቢሮዎችና አንድ ከተማ አስተዳደር ከነገ ጀምሮ ለመተግበር ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል። የፋይናንስ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት፣ ውሃና ማዕድን፣መንገድና ትራንስፖርት ልማት፣ ገቢዎች ቢሮዎችና የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት ተግባራዊ ከሚደረግባቸው መካከል የጠቀሷቸው ናቸው። ስርዓቱ የሚባክኑ ሀብቶች ለማዳን የሚያስችል ምቹ መደላድል መሆኑን አንስተው፤ የፋይናንስ ግልጸኝነትና ተጠያቂነትን በማስፈን በህዝብና መንግስት መካከል መተማመን እንደሚያጎለብት አስረድተዋል። በተለይም በመንግስት መስሪያ ቤቶች ከጨረታ ሂደት ጋር በተያያዘ ያለውን የወረቀት ንኪክና የጊዜና ጉልበት እንዲሁም አለአግባብ የሚወጡ የተለያዩ ወጪዎችን ማስቀረት የሚያስችል አሰራር መሆኑን ጠቁመዋል። ከዚህ ባለፈ ክልሉ የፋይናንስ ግልጸኝነትን ለማጠናከር ከ45 በላይ የመንግስት ተቋማት የ"ኦን ላይን " አሰራር በመዘርጋቱ ውጤት እየተገኘ መሆኑን ገልጸው፤ በቀጣይም ቼክ አልባ አሰራር ለመዘርጋት ከባንኮች ጋር እየሰሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ከቢሮው ጋር ስምምነቱን የተፈራረመው ፔራጎ ኢንፎርሜሽን ኃ.የተ.ግ.ማ. የተሰኘው የሶፋትዌር ድርጅት ሃላፊ አቶ እውነቱ አበራ፤ የዘመናዊና ቀልጣፋ የፋይናንስ አሰራር ለመዘርጋት የሚያስችል ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ይህም በመንግስት ግዥ የሚወዳደሩ ተቋማት ያለቦታ ገደብ እኩል በሆነ አሰራር ተጠቃሚ መሆን እንዲችሉ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። የፋይናንስ ህግ በአግባቡ እንዲተገበር፣የጊዜና ጉልበት ብክነት ከመቀነስ ባለፈ ከተለያዩ አማራጮች ጋር ተቀናጅቶ በመስራት ለጨረታና መሰል ግዥዎች ላይ የሚነሱ ቅሬታዎችን የሚያስቀር መሆኑን አመላክተዋል። የፌዴራል ግዥና ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀጂ ኢብሳ በበኩላቸው፤ የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓትን መተግበር በፋይናንስ አሰራር ላይ የሚነሱ ቅሬታዎች ለማስወገድ እንደሚያስችል ገልጸዋል። እንዲሁም “ግልጽነትና ተጠያቂነትን በማስፈን፣ ብልሹ አሠራርን በማስወገድ ፣በመንግስትና በህዝብ መካከል መተማመን እንዲኖር ያደርጋል" ብለዋል። እንደሀገር ዘርፉን ለማጠናከር እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ የሲዳማ ክልል መተግበሪያውን በመጠቀም የዘመነ የፋይናንስ አሰራር ለመከተል እንደተዘጋጀ መረዳታቸውን ጠቅሰዋል። በክልሉ ይህን ተግባራዊ ለማድረግ እንዲቻል ከሐምሌ 2015 ዓም ጀምሮ ለተመረጡ ቢሮዎች ባለሙያዎች ስልጠናዎች ሲሰጡ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። እንደ ሀገር አሁን ላይ 163 ፌዴራል መስሪያ ቤቶች የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ስርዓት መተግበር ጀምረው የታለመለት ውጤት እየተገኘ መሆኑን አንስተው፤ ወደ ሌሎች ክልሎች የማስፋት ስራ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል ።
የኢትዮጵያን የዲጂታል ሉዓላዊነት ለማስከበር የዜጎችና የተቋማት ጥረት ወሳኝ ነው-የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር
Nov 13, 2023 168
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 3/2016 (ኢዜአ) ፦ የኢትዮጵያን የዲጂታል ሉዓላዊነት ለማስከበር የዜጎችና የተቋማት በግንዛቤ ላይ የተመሰረተ ጥረት ወሳኝ መሆኑን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ገለጸ። አገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር የህብረተሰቡን ንቃት ህሊና ከፍ የሚያደርጉ ተግባራትን በማከናወን በስኬት መጠናቀቁንም አስታውቋል። የአስተዳደሩ ዋና ዳይሬክተር ሰለሞን ሶካ ከጥቅምት 1-30/2016 ዓ.ም " አይበገሬ የሳይበር አቅም ለሀገር ሉዓላዊነት " በሚል መሪ ሀሳብ የተከበረውን አገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወርን አስመልክተው ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም ወሩ የህብረተሰቡን የሳይበር ደህንነት ግንዛቤ ከፍ የሚያደርጉ ዝግጅቶች የቀረቡበት ነው ብለዋል፡፡ ህብረተሰቡ ላይ የሚፈጠረው ንቃተ ህሊና ለአገር የሳይበር ደህንነት ተጨማሪ አቅም ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ በፋይናንስ፣ ቁልፍ መሰረተ ልማት፣ መንግስታዊ እና መንግስታዊ ያልሆኑት ተቋማት ላይ የሳይበር ደህንነትን ለማረጋገጥ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ ተቋማት የሳይበር ደህንነት ንቅናቄውን በመቀላቀል የመከላከል ዝግጁነታቸውን እንዲያሻሽሉ ማስቻሉን እና የግሉ ዘርፍ ተሳትፎን ማነቃቃቱንም ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያን የዲጂታል ሉዓላዊነት ለማስከበር የዜጎችና የተቋማት በግንዛቤ ላይ የተመሰረተ ጥረት ወሳኝ መሆኑንም አስረድተዋል። የሀገሪቱን የሳይበር ምህዳር በአስተማማኝ ሁኔታ የሚያስጠብቁ ወጣቶችን ከማፍራት አንጻር መነቃቃት መፈጠሩን ገልጸው፤ የሳይበር ደህንነትን ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በርካታ የምርምር ውጤቶች፣ ወቅታዊ መረጃዎች፣ የአፈጻጸም ሪፖርቶችና የግንዛቤ መልዕክቶችም በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች ለህብረተሰቡ ተደራሽ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል፡፡ መገናኛ ብዙሃን፣ ቢልቦርድ፣ ማህበራዊ ሚዲያ፣ ዲጂታል ስክሪኖች እና ሌሎችም ዘዴዎች መልዕክቶቹ ተደራሽ ከተደረጉባቸው መካከል ናቸው ብለዋል፡፡ በሳይበር ደህንነት ወር ስውር ውጊያ የተሰኘ ፊልም መመረቁ፣ በርካታ ሰዎች የተገኙበት አውደ ርእይ መዘጋጀቱ እንዲሁም ግንዛቤን ከፍ የሚያደርጉ ውይይቶች መካሄዳቸውን የጠቀሱት ዋና ዳይሬክተሩ፤ በጥቅሉ ስኬታማ ነበር ብለዋል።