ሳይንስና ቴክኖሎጂ
በኢትዮጵያ አለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያረጋግጡ የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ስራዎችን የሚያጎለብቱ የአሰራር ማሻሻያዎች እየተደረጉ ነው
Apr 26, 2024 62
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንድትሆን የሚያስችሉ የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ስራዎችን የሚያጎለብቱ የአሰራር ማሻሻያዎችን እያደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለስልጣን አስታወቀ። በኢትዮጵያ ጠንካራ ብሔራዊ የአዕምሯዊ ንብረት አስተዳደርን መገንባት የሚያስችሉ የአዋጅ ማሻሻያዎች እየተከናወኑ መሆኑም ተገልጿል። የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለስልጣን በአለም ለ24ኛ በኢትዮጵያ ለ22ኛ ጊዜ የሚከበረውን ዓለም አቀፍ የአዕምሯዊ ንብረት ቀን በሳይንስ ሙዚየም አክብሯል። ቀኑ ''አዕምሯዊ ንብረት ለዘላቂ ልማት መጪው ጊዜያችንን በኢኖቬሽንና ፈጠራ መገንባት'' በሚል መሪ ሃሳብ በፈጠራ ስራዎች አውደ ርዕይና በፓናል ውይይት ነው የተከበረው። የፈጠራ አውደ ርዕዩን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን አለማየሁ(ዶ/ር)፣ የፍትህ ሚኒስትር ዴኤታ ኤርሚያስ የማነብርሃን (ዶ/ር) እንዲሁም የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል ከፍተውታል። በዚህ ወቅት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን አለማየሁ(ዶ/ር) እንዳሉት ኢትዮጵያ የዘላቂ ልማት ግቦችን ለማሳካት በቁርጠኝነት እየሰራች ሲሆን በአንዳንድ ዘርፎች የተሻሉ ውጤቶች ተመዝግበዋል። ከዚህ ቀደም የፈጠራ ስራ ባለቤቶች ሃሳባቸውን ወደ ተግባር ለመቀየር የሚገድቧቸው የህግ ማዕቀፍና ፋይናንስን የመሳሰሉ ችግሮች እንደነበሩ አንስተዋል። ይህም የፈጠራ ስራዎች እንዳይበራከቱና ዘርፉ ለኢኮኖሚው የሚጠበቅበትን አስተዋፅኦ እንዳያበረክት ተግዳሮት ሆኖ መቆየቱን ተናግረዋል። አሁን ላይ በአገሪቱ ለፈጠራ ስራ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የህግ ማዕቀፍ ከማሻሻያ ጀምሮ ለስታርት አፖች ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር በርካታ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ገልፀዋል። መንግስት ስታርት አፖች ለሀገሪቱ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ሞተር ሆነው እንዲዘልቁ ብሎም ፈጠራና አዳዲስ ግኝቶች የሚያፈልቅባቸው የጥራት ማዕከል እንዲሆኑ በትጋት እየሰራ ይገኛል ነው ያሉት። የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል መንግስት ጠንካራ ብሄራዊ የአዕምሯዊ ንብረት አስተዳደር ለመገንባት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።   በፍጥነት በሚለዋወጥ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሁኔታ በመኖሩ ቀጣይነት ያለው የለውጥ ስራ ማከናወን ይጠይቃል ነው ያሉት። ባለስልጣኑ ይህን በመገንዘብ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የስትራቴጂና የህግ ማዕቀፍ ማሻሻያዎችና ተቋማዊ ሪፎርም እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል ። ዋና ዳይሬክተሩ በአሁኑ ወቅት ሶስት አዋጆችን የማሻሻል እንዲሁም ሁለት አዳዲስ አዋጆችን እየተረቀቁ መሆኑን ተናግረዋል። ዘርፉ የቴክኖሎጂና የፈጠራ ሽግግር ለማምጣት የሚያስችል ቢሆንም እስካሁን ባለው ሁኔታ ብዙ እንዳልተሰራበት ነው የገለፁት። አሁን ላይ በስታርት አፕ ዙሪያ የተጀመረው ስራ የህብረተሰብ ችግር የሚፈቱ የፈጠራ ሃሳቦች ተግባር ላይ እንዲውሉ ያግዛል ብለዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣናና የአለም ንግድ ድርጅት አባልነትን ስትቀላቀል ተወዳዳሪ ሆና እንድትቀጥል የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ስራዎች መበራከት አለባቸው ብለዋል። ባለስልጣኑ የሚሰራባቸውን ህጎች ከዘመኑ የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ደረጃ ጋር ተመጣጣኝ ለማድረግ የአሰራር ማሻሻያ እያደረገ መሆኑንም አስረድተዋል። በአውደርዕዩ የፈጠራ ስራቸውን ይዘው የቀረቡ የፈጠራ ባለቤቶች በበኩላቸው የአዕምሯዊ ንብረት ከፈጠራ ባለቤቱ ባሻገር ለአገር ኢኮኖሚ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል።   መጸዳጃ ቤትን በንፅህና ለመጠበቅ የሚያስችልና ደረቅና ፈሳሽ ቆሻሻን መለየት የሚያስችል ቴክኖሎጂ ይዘው የቀረቡት በአርሲ ዩኒቨርሲቲ የህብረተሰበ ጤና አጠባበቅ መምህር ዶክተር ግዛቸው አብደታ እንዳሉት የአዕምሯዊ ንብረት ጥበቃ ለአገር ኢኮኖሚ ከፍተኛ ሚና አለው።   መምህር በሌለበት ጊዜ ማስተማር የምትችል ሮቦት ይዞ የቀረበው ወጣት በረከት ጌቱ በበኩሉ የፈጠራ ባለቤትነት መብት መሰጠቱ የፈጠራ ባለቤትነት ደህንነትን ከማስጠበቅ ባሻገር ስራን በማሻሻል አገርን ለመደገፍ ያግዛል ብሏል።  
ቲምቡክቱ ኢኒሼቲቭ በኢትዮጵያ ስራ መጀመሩ ስታርትአፖችን ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ የተያዘው ቁርጠኝነት ያግዛል
Apr 26, 2024 67
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ቲምቡክቱ ኢኒሼቲቭ ስራ መጀመሩ ስታርት አፕንና የስራ ፈጠራ እንዲጎለብት ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው ሲሉ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር በለጠ ሞላ ተናገሩ። በአፍሪካ የስራ ፈጠራና ስታርትአፕን የሚደግፈው ቲምቡክቱ ኢኒሼቲቭ በኢትዮጵያ በትላንትናው እለት ስራውን በይፋ ጀምሯል። ኢኒሼቲቩ በተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም አነሳሽነት በአፍሪካ በተለይ ኢንቨስትመንትን፣ ስራ ፈጠራንና ስታርት አፕን ለመደገፍ የሚሰራ ነው። በኢንሼቲቩ ማስጀመሪያ መርሀ ግብር ላይ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር በለጠ ሞላ፣ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ብሩክ ታዬ፣ የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም የአፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር አሁና ኢዚያኮንዋ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር በለጠ ሞላ ቲምቡክቱ ኢኒሼቲቭ በሀገራችን መጀመሩ የስራ ፈጠራና ስታርትአፕን እንዲጎለብት ትልቅ አቅም የሚፈጥር እንደሆነ ገልጸዋል። ኢንሼቲቩ በአፍሪካውያን መካከል ያለውን የኢኖቬሽን ስነ-ምህዳርን ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ አቅም የሚፈጥር ነው ብለዋል። በቀጣይም የዜጎችን የፈጠራ አቅም ለማጎልበት እና ዲጂታልን የመጠቀም ባህል ለማጎልበት ሚኒስቴሩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራ ገልፀል። የስራ ፈጠራና ስታርት አፕን ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ አላማ ይዞ እየሰራ የሚገኘውን የቲምቡክቱ ኢኒሼቲቭን ከግብ ለማድረስ ከአጋር ድርጅቶች ጋር የጀመራቸውን የጋራ ስራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ሚኒስትሩ አክለዋል። የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ብሩክ ታዬ በበኩላቸው ኢኒሸቲቩ ስታርትአፖች በጋራ ሆነው በዘርፉ ላይ በመስራት ለውጥ እንዲያመጡ አቅም የሚፈጥር ነው ብለዋል። መንግስት በሀገሪቱ ስራ ፈጠራን ለማበረታታት ብሎም የቲምቡክቱ ኢንሼቲቭን ወደ ተግባር ለመቀየር ፖሊሲዎችን ከማዘጋጀት ጨምር ሌሎች በርካታ ስራዎችን እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም የኢትዮጵያ ተጠሪ ዶክተር ሳሙኤል ዶ በበኩላቸው ኢትዮጵያ የዲጂታል ዘመንን ለመገንባት የምታደርገው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። ኢንሺቲቩ አፍሪካውያን በጋራ እንዲሰሩ ያግዛል ብለዋል።    
የኢትዮጵያን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ዘርፍ  ወደተሻለ ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ የቴክኖሎጂ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል-- የፌደራል  ተቋማት የሱፐርቪዥን ቡድን 
Apr 25, 2024 106
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ዘርፍ ወደተሻለ ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ የቴክኖሎጂ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ የፌደራል ተቋማት የሱፐርቪዥን ቡድን ገለጸ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የበጀት ዓመቱን የመንግሥት የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ሲገመግሙ የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን ተቋቁሞ ትኩረት በተሰጣቸው ዘርፎች ላይ የመስክ ምልከታ እንዲያደርግ አቅጣጫ ማስቀመጣቸው ይታወሳል። በዚህም የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የሚያስተባብረው የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴርን የስራ እንቅስቃሴ ተመልክቷል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የኢኖቬሽን አማካሪና የሱፐርቪዥን ቡድኑ አስተባባሪ ዶክተር ሰለሞን በላይ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ በሎጅስቲክስ፣ በትራንስፖርት፣ በታዳሽ ኃይል እና በቴክኖሎጂ አጠቃቀም ላይ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች አበረታች ናቸው። በአንጻሩ እንደ ሀገር ትኩረት የሚፈልጉ የፖሊሲ እና የህግ ማሻሻያ የሚጠይቁ የመንግስትን ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች መኖራቸውን አመላክተዋል። ለአብነትም የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ እና የማበረታቻ ስርዓት ሊታዩ የሚገባቸው ጉዳዮች መሆናቸውን ጠቁመዋል። የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ዘርፉን ለማሳለጥ እየተከናወኑ ያሉ የቴክኖሎጂ አሰራሮች እና የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ጠቁመዋል።   የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ደኤታ በርኦ ሀሰን ዲጂታላይዜሽን ለዘርፉ አዲስ የዕድገት ምዕራፍ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፥ እስካሁን በተተገበሩ የቴክኖሎጂ ስራዎች ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ከዘርፉ የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ላይ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ለሱፐርቪዥን ቡድኑ ገልጸዋል።   ዘርፉን ለማሳደግ ሁሉም አይነት ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ደንጌ ቦሩ ናቸው። በዚህም የሎጂስቲክ ዘርፉን አፈጻጸም ማሳደግ መቻሉን እና ከዚህ የበለጠ ውጤት እንዲመዘገብ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።    
በስታርትአፕ ዐውደ ርዕይ የቀረቡ የፈጠራ ሀሳቦችና ቴክኖሎጂዎች ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር ትልቅ ተስፋ ሰጭ ናቸው
Apr 25, 2024 109
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- በስታርትአፕ ዐውደ ርዕይ የቀረቡ የፈጠራ ሀሳቦችና ቴክኖሎጂዎች ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር ትልቅ ተስፋ ሰጭ እንደሆኑ የኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሽመልስ እሸቱ ገለጹ። ከመጋቢት 30 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ በሳይንስ ሙዚየም የተከፈተው የስታርትአፕ ኢትዮጵያ ዐውደ ርዕይ በተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችና የተቋማት ኃላፊዎች እየተጎበኘ ነው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የዐውደ ርዕዩ ጎብኝዎች እንዳሉት በስታርትአፖች የቀረቡ የፈጠራ ስራዎች የኢትዮጵያን መፃዒ ዕድል ብሩህ የሚያደርጉ ናቸው። የኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ሽመልስ እሸቱ በዐውደ ርዕዩ በቴክኖሎጂ የታገዘ ዕድገት እንዲመዘገብ የሚያስችሉ ፈጠራዎችን መመልከታቸውን። የስታርትአፕ የፈጠራ ስራዎች በአግባቡ ከታገዙ የበለጸገች ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ ተስፋ ሰጭ እንደሆኑ ጠቅሰው፤ ኮርፖሬሽኑ ቴክኖሎጂዎች ገቢራዊ እንዲሆኑ የራሱን ሚና እንደሚወጣ አረጋግጠዋል። ሀገራዊ ልማቱ ዘመኑን በዋጁ ቴክኖሎጂዎች መደገፍ እንደሚገባ ገልጸው፤ በዐውደ ርዕዩ የቀረቡ የፈጠራ ስራዎችም የተቋማትን ምርትና አገልግሎት የሚያዘምኑና የሚያቀላጥፉ እንደሆኑ ጠቁመዋል። ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመጡት አቶ ተስፋ አበባና በአዲስ አበባ የልደታ ማኑፋከቸሪንግ ኮሌጅ ተማሪዋ ማህሌት ገብሬ እንዳሉት የስታርትአፕ ቴክኖሎጂዎች ሀገርን ወደ ተሻለ ልማት ያሸጋግራሉ። ስታርትአፕን መደገፍ ለወደፊቷ ኢትዮጵያ መጻኢ ዕድል ካለው ቁልፍ ፋይዳ አኳያ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ገልጸው፤ ለዚህም የፈጠራ ክህሎት ያላቸውን ወጣቶች ይበልጥ ማበረታታት ይገባል ነው ያሉት። ለዕይታ የቀረቡ የቴክኖሎጂ ውጤቶች የነገዋ ኢትዮጵያን ለማዘመን ብሩህ ተሰፋ እንደሆኑ ጠቁመዋል። የስታርትአፕ ዐውደ ርዕዩ እስከ ሚያዝያ 20 ቀን 2016 ዓ.ም ይቀጥላል። በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርት፣ በኢነርጂ፣ በኢንዱስትሪ፣ በፋይናንስና በሌሎች ዘርፎች የተሰማሩ 500 የሚጠጉ ስታርትአፖች እየተሳተፉ ነው።    
በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዘርፍ ተወዳዳሪ የሆኑ ታዳጊዎችን ለማፍራት በትኩረት እየተሰራ ነው -  ኢንስቲትዩቱ
Apr 25, 2024 151
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዘርፍ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ታዳጊዎችን ለማፍራት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ገለጸ። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በመጪው ክረምት የስልጠና መርሐ ግብር የሚሳተፉ ተማሪዎችን ምዝገባ ጀምሯል። በ3ኛ ዙር ስልጠና የሚሳተፉት የመጀመሪያና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ የሆኑ እና በሳምንት ለ4 ቀናት መከታተል የሚችሉ መሆን እንደሚኖርባቸው ተገልጿል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ወርቁ ጋቸና፤ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የዓለም አቀፍ የኢኮኖሚና ቴክኖሎጂ ዕድገት መለኪያ የሆነ ዘርፍ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያም ግንባር ቀደም አህጉራዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ተቋም በመገንባት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በመስኩ የፈጠራ ዝንባሌ እና ክህሎት ላላቸው ታዳጊዎች የሚሰጠው ስልጠናም በዘርፈ ብዙ መስኮች ተወዳዳሪ ሀገር መፍጠር የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በመጪው ክረምት ታዳጊ ተማሪዎችን በመቀበል በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዘርፍ ክህሎታቸውን በማበልጸግ የተሻለ ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ስልጠና ለመስጠት በቂ ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል። ስልጠናውም የኢትዮጵያን ከፍታ በማስቀጠል ፈጠራና ክህሎትን በማበረታታት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሆኑ ታዳጊዎችን ማፍራት የሚያስችል መልካም አጋጣሚ መሆኑን አስረድተዋል።   በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የምርምርና ልማት ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ታዬ ግርማ (ዶ/ር)፥ በክረምት ወራት የሚሰጠው ስልጠና እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በቀጣይም በኢንስቲትዩቱ ከሚሰጠው ስልጠና በተጨማሪ በክልሎች ለማስፋት ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።   የቴክኖሎጂ አማካሪው ሰለሞን ሙሉጌታ፥ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ የሚሰጥ ስልጠና ታዳጊዎች የዓለምን አዝማሚያና ዝንባሌ በቅጡ እንዲረዱ የሚያስችል ነው ብለዋል። የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዕውቀትንም ለግብርና፣ ለመንግስት አገልግሎት፣ ለጤና እና ሌሎች ተግባራት እንዲያውሉት ማስተማር እንደሚያስፈልግ አስገንዝቧል። በመጪው ክረምት ለሁለት ተከታታይ ወራት በሚሰጠው ስልጠና ፍላጎት ያላቸው ታዳጊዎች ከሚያዝያ 17 እስከ ግንቦት 07/2016 ባሉት ቀናት መመዝገብ እንደሚችሉ ተገልጿል። ከሀምሌ 1 እስከ ጳጉሜ 1/2016 ዓ.ም በሚቆየው ስልጠና ተማሪዎች በሰው ሰራሽ አስተውሎት እውቀትና ክህሎት የሚያገኙበት የንድፈ ሀሳብና የተግባር ትምህርት ይሰጣቸዋል። ስልጠናው ከሚያተኩርባቸው መካከል የሰው ሰራሽ አስተውሎት መሰረታውያን፣ ሮቦቲክስ፣ ፕሮግራሚንግ፣ ማሽን ለርኒንግ እና ሌሎችም ይገኙበታል።  
በአዳማ እና ቢሾፍቱ የተጀመረውን የስማርት ከተማ ግንባታ ወደ ሌሎች የሀገሪቱ ከተሞች ማስፋፋት ይገባል- የፌደራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን 
Apr 25, 2024 92
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር በአዳማ እና ቢሾፍቱ ከተሞች የተጀመረውን የስማርት ከተማ ግንባታ ወደ ሌሎች የሀገሪቱ ከተሞች ማስፋፋት እንዳለበት የፌደራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን አስታወቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የበጀት ዓመቱን የመንግሥት የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ሲገመግሙ የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን ተቋቁሞ ትኩረት በተሰጣቸው ዘርፎች ላይ የመስክ ምልከታ እንዲያደርግ አቅጣጫ ማስቀመጣቸው ይታወሳል። በዚህም የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የሚያስተባብረው የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር የስማርት ከተማ ግንባታ ሂደት ያለበትን ደረጃ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ፣ በአዳማ ከተማ እና በቢሾፍቱ ከተማ በመገኘት የመስክ ምልከታ አድርጓል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ፈንታ ደጀን በዚሁ ወቅት፥ መንግስት በ10 ዓመትና በመካከለኛ ዘመን ዕቅዱ ለስማርት ከተማ ግንባታ ትኩረት መስጠቱን ገልጸዋል። የስማርት ከተማ ስትራቴጂ በማዘጋጀት ለክልሎች እና ከተሞች ተደጋጋሚ የግንዛቤ ማስጨበጥ ስልጠና በመስጠት በ2015 ዓ.ም አዳማ ከተማን እንደ ሞዴል በመውሰድ ወደ ተግባር መገባቱን አስረድተዋል። ከስማርት ከተማ ግንባታ ምሰሶዎች ውስጥ ለ”ስማርት አስተዳደር” ቅድሚያ በመስጠት እየተሰራ ነው ብለዋል። ክልሎችም ከተሞቻቸውን ስማርት ለማድረግ ተነሳሽነት እያሳዩ እንደሆነ ገልጸው በጅማ፣ ባህር ዳር፣ ደብረ ብርሃን፣ ደሴ፣ ሆሳዕና፣ ቡታጂራ፣ አርባምንጭ እና ወላይታ ሶዶ ጅምር ስራዎች እንዳሉ ተናግረዋል።   የአዳማ ከተማ ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ በከተማዋ የተጀመረው የዲጂታላይዜሽን ስራ ውጤት እያመጣ መሆኑን ተናግረዋል። አገልግሎትን ከማቀላጠፍ ባሻገር የመንግስትን የማስፈፀም አቅም እንዲጎለብትና ብልሹ አሰራሮች እንዲቀንሱ አድርጓል ነው ያሉት።   የቢሾፍቱ ከተማ ከንቲባ አቶ አለማየሁ አሰፋ በከተማዋ የአገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታል ለማድረግ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል። የከተማ መሬት ይዞታን ወደ ካዳስተር በማስገባት የይዞታ ማረጋገጫ በኦንላይን መከናወኑን አንስተው፥ ይህም የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎትን እንደሚያቀላጥፍ ጠቅሰዋል።   የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን መሪ አቶ ተገኔ ኃይሉ በአዳማና በቢሾፍቱ ከተሞች ያለው የቴክኖሎጂና የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ትግበራ የሚበረታታ ነው ብለዋል። በከተሞቹ የመሬት ይዞታዎችን ወደ ካዳስተር የማስገባት እና የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ምዝገባን በኦን ላይን መፈጸሙ የስማርት ከተማ ግንባታን የሚያግዝ እንደሆነ አንስተዋል። የከተማ አገልግሎቶችን በዲጂታል መስጠት መጀመራቸውም ተጠናክሮ መቀጠል የሚገባው እንደሆነ ገልጸዋል። በአዳማና ቢሾፍቱ ወንጀልን ለመከላከል እና የትራፊክ ፍሰትን ለመቆጣጠር የ"ስማርት ሴኪዩሪቲ" ቴክኖሎጂ ከተቋማት ጀምሮ በዋና ዋና ጎዳናዎች መተግበሩ የሚበረታታ ነው ብለዋል።   የሱፐርቪዥን ቡድኑ አባል አቶ አሸናፊ አበበ በበኩላቸው፥ ባለሙያዎችን በማብቃትና የዲጅታል መሰረተ ልማቶችን በማልማት አገልግሎቶችን ለማሳለጥ የጀመሩት ስራ መጠናከር አለበት ብለዋል። በሁለቱ ከተሞች ያለውን ውጤታማ ተሞክሮ በሌሎች ከተሞች ማስፋፋት እንደሚገባም ጠቁመዋል።        
የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በክረምት የስልጠና መርሃ ግብር የሚሳተፉ ተማሪዎችን ምዝገባ ጀመረ
Apr 25, 2024 78
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በመጪው ክረምት የስልጠና መርሃ ግብር የሚሳተፉ ተማሪዎችን ምዝገባ ጀመረ። ኢንስቲትዩቱ የስልጠና መርሐግብሩንም ይፋ አድርጓል። በሶስተኛ ዙር የክረምት ስልጠና መርሃ ግብር የሚሳተፉት የመጀመሪያ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ የሆኑ እና ስልጠናውን በሳምንት ለ4 ቀናት መከታተል የሚችሉ መሆን እንደሚጠበቅባቸው ገልጿል።   በመጪው ክረምት ለተከታታይ ሁለት ወራት ለሚሰጠው ስልጠናም ፍላጎት ያላቸው ታዳጊዎች ከዛሬ ሚያዝያ 17 እስከ ግንቦት 07/2016 ባሉት ተከታታይ ቀናት መመዝገብ እንደሚችሉ አስታውቋል። ስልጠናው ከሀምሌ 1 እስከ ጳጉሜ 1/2016 ዓ.ም ለሁለት ወራት የሚቆይ ሲሆን በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዙሪያ የንድፈሀሳብና የተግባር ትምህርት ለሰልጣኝ ተማሪዎች ይሰጣል ተብሏል። ስልጠናው ከሚያተኩርባቸው መካከል የሰው ሰራሽ አስተውሎት መሰረታውያን፣ ሮቦቲክስ፣ ፕሮግራሚንግ፣ ማሽን ለርኒንግ እና ሌሎችም ይገኙበታል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ወርቁ ጋቸናን ጨምሮ የኢንስቲትዩቱ የስራ ኃላፊዎች፣ አሰልጣኞችና ተማሪዎች መርሐግብሩ ይፋ ሲደረግ ተገኝተዋል።  
ኢትዮ ቴሌኮም የዲጅታል ኢኮኖሚ ግንባታን ለማፋጠን እየሰራ መሆኑን ገለፀ
Apr 25, 2024 152
ሀዋሳ/ባህር ዳር፤ ሚያዚያ 17/2016 (ኢዜአ)፡- ኢትዮ ቴሌኮም የዲጅታል ኢኮኖሚ ግንባታን ለማፋጠን እየሰራ መሆኑን አስታወቀ። ለ32 ሚሊዮን ዜጎች የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዘገባ ለማካሄድ ተግባራዊ እንቅሰቃሴ ውስጥ መግባቱንም አስታወቋል። ቴሌኮሙ የብሄራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ በደቡብ ሪጂን በሀዋሳ ከተማ ትላንት ባስጀመረበት ወቅት የኢትዮ ቴሌኮም ኢንፎርሜሽን ሲስተም ቺፍ ኦፊሰር አቶ እንዳለ አስራት እንደገለጹት ኢትዮ ቴሌኮም የዲጅታል ኢኮኖሚ ግንባታን ለማፋጠን እየሰራ ይገኛል። ለዚህም መጠነ ሰፊ የመሰረተ ልማት ማስፋፊያ ሥራዎችን በመዘርጋት እንዲሁም አዳዲስ ዘመናዊ የዲጅታል መፍትሄዎችን እያስተዋወቀ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ የዲጅታል ኢኮኖሚ ግንባታን ለማፋጠን ሁሉን አቀፍ የቴሌኮምና የዲጅታል ፋይናንሻል አገልግሎት ተደራሽ እያደረገ እንደሚገኝ አውስተዋል።   በዚህ ረገድ የብሄራዊ ዲጅታል መታወቂያ የዲጅታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂን እውን ለማድረግ ከሚያስፈልጉ አስቻይ ሲስተሞች ውስጥ አንዱ መሆኑን አስረድተዋል። ኩባንያው በትላንትናው እለት በሀገር አቀፍ ደረጃ ብሄራዊ ዲጅታል መታወቂያ አዲስ አበባን ጨምሮ በ30 ከተሞች በይፋ መመዝገብ ማስጀመሩን ገልፀዋል። በቀጣይም በሌሎች የሀገሪቱ ከተሞች የዲጅታል መታወቂያ አገልግሎቱ እንደሚጀመር ጠቁመዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ እስከ 2018 ዓ.ም ድረስ 90 ሚሊዮን ለሚሆኑ ዜጎች መታወቂያውን ለማዳረስ መታቀዱን ጠቁመው ከዚህ ውስጥ ቴሌኮም ለ32 ሚሊዮን ዜጎች ተደራሽ ያደርጋል ብለዋል። "በዚህም የሀገራዊ እቅዱን 36 በመቶ የሚያከናወን ይሆናል" ያሉት አቶ እንዳለ ለዚህም ተፈጻሚነት በወር በዓማካይ 1 ሚሊዮን ዜጎችን ለመመዝገብ መታቀዱን አስታውቀዋል።   የዲጅታል መታወቂያ ከዜጎች በሚወሰዱ መለያ አማካይነት የተረጋገጠ መረጃ ለማቅረብ የሚያስችል ሲሆን ይህም ለቀልጣፋ ለአካታች የማህበራዊና ኢኮኖሚ እድገትና ለቢዝነስ ትስስር ፋይዳው የጎላ መሆኑን አስረድተዋል። በመሆኑም ዜጎች ማንነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ እንደ ቀበሌ መታወቂያ፣የታደሰ መንጃ ፍቃድ፣ፓስፖርት፣ያሉ ሰነዶችን በመያዝ ወይንም የሰው ምስክር በማቅረብ በነፃ መመዝገብ እንደሚችሉ አስታውቀዋል። በተመሳሳይ የኢትዮ ቴሌኮም የሰሜን ምእራብ ሪጅን ብሔራዊ የዲጅታል መታወቂያ ማስጀምሪያ መርኃ-ግብር ትናንት በባህር ዳር ከተማ ተካሂዷል። የኢትዮ ቴሌኮም የዞንና የሪጅን ኮርዲኔሽን ዲፒውቲ ችፍ ኦፊሰር አቶ ሃይለሚካኤል ነቃ ጥበብ እንደገለጹት ኢትዮ ቴሌኮም የህብረተሰቡን የግንኙነት ስራ ከማሳለጥ ባሻገር ዘመናዊነት የሚያሳልጡ ስራዎች እያከናወነ ነው። ከነዚህ ስራዎች መካከል ብሔራዊ የዲጅታል መታወቂያ ማዘጋጀት አንዱ መሆኑን ጠቁመዋል። በሰሜን ምእራብ ሪጅን የብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ለመስጠት የሚያስችል የቅድመ ዝግጅት አሰራሮች ተጠናቀው ወደ ስራ መገባቱን የገለጹት ደግሞ የሪጅኑ ኦፕሬሽን ዳይሬክተር አቶ አበበ ጥሩነህ ናቸው። "ኢትዮ ቴሌኮም አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ለህብረተሰቡ በማስተዋወቅ የእለት ተእለት ስራዎችን ቀላልና ቀልጣፋ በማድረግ የጎላ ሚና እየተወጣ ይገኛል" ብለዋል። በባህር ዳር ከተማ የተጀመረው የስራ እንቅስቃሴም በቅርቡ በደብረ ማርቆስ፣ ፍኖተ ሰላም፣ ኮሶበር፣ ሞጣ፣ ቢቸናና ሌሎችም ከተሞች እንደሚጀመር አስታውቀዋል።        
በመላ ሀገሪቱ በተመረጡ የኢትዮ ቴሌኮም አገልግሎት መስጫ ማዕከላት የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ተጀመረ
Apr 24, 2024 299
ሐረር/ጅማ/አሶሳ/ድሬዳዋ/ሶዶ/ነቀምቴ/አዳማ/ጋምቤላ፤ ሚያዝያ 16 / 2016 (ኢዜአ)፡- ኢትዮ ቴሌኮም በመላ ሀገሪቱ በተመረጡ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላት የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር አካሂዷል። የተቋሙ የብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ምዝገባ ማስጀመሪያ መርሃግብሩ የተካሄደባቸው ሐረር፣ ጅማ፣ አሶሳ፣ ድሬዳዋ፣ ወላይታ ሶዶ፣ ነቀምቴ፣ አዳማና ጋምቤላን ጨምሮ በ29 ዋና ዋና ከተሞች መሆኑ ተገልጿል። በሐረር በተካሄደው የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ በኢትዮ-ቴሌኮም የማዕከላዊ ምስራቅ ሪጅን ዳይሬክተር አቶ መሐመድ ሰዒድ እንዳሉት፤ ዛሬ የተጀመረው የብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ምዝገባ በሐረሪ ክልልና በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ባሉ 28 የአገልግሎት መስጫ ማዕከላት ይሰጣል።   በተመሳሳይ ኢትዮ-ቴሌኮም የደቡብ ምዕራብ ሪጅን የዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ለመስጠት የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ዛሬ በጅማ ከተማ ተካሄዷል። የደቡብ ምእራብ ሪጅን ኦፕሬሽን ዳይሬክተር አቶ ክፍሌ ካሳ በብሄራዊ የዲጂታል መታወቂያ ማስጀመሪያ መርሀግብር እንደገለጹት፤ ግልጽና አካታች አሰራርን ለማስፈን፣ የሳይበር ማጭበርበርን ለመከላከልና የተሻለ አገልግሎትን ለመስጠት ብሎም የዜጎችን የአኗኗር ደረጃ ለመቀየር ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያው ጉልህ ድርሻ አለው። ተቋሙ በአሶሳም የምዝገባ አገልግሎቱን ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በተመሳሳይ መካሄዱን አመልክተዋል፡፡ በኢትዮ- ቴሌኮም የምዕራብ ምዕራብ ሪጅን ኦፕሬሽን ዳይሬክተር አቶ ጥላሁን እጅጉ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ የማህበረሰቡን የእለት ተዕለት ኑሮ በማቀላጠፍ እና የተቋማትን አሰራር በማዘመን ረገድ ጉልህ ድርሻ አለው። ለዚህም ማሳያው ደግሞ ለዜጎች አገልግሎት የዲጂታል ግብይት ማቀላጠፉ፣ የፋይናንስ አካታችነትን የሚጨምሩ የብድር አገልግሎት ዋስትና አገልግሎት ማግኘት ማስቻሉን በአብነት ጠቅሰዋል፡፡ የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ አገልግሎት በድሬደዋም በይፋ ተጀምሯል። የምዝገባ ማስጀመሪያ መርሃግብሩን በድሬዳዋም ባካሄደበት ወቅት የኢትዮ-ቴሌኮም የኔትወርክ ኦፕሬሽን ማዕከል ቺፍ ኦፊሰር አቶ አበበ አምባው ተቋሙ ዲጂታል ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ እያካሄዳቸው ባሉት ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶችና ለውጦች እያስመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል። በወላይታ ሶዶ ማዕከል ላይ የተከናወነውን መርሃግብር ያስጀመሩት የኢትዮ ቴሌኮም ቺፍ ፋሲሊቲና ፍሊት ኦፊሰር አቶ አይናለም አልበኔም ፤ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ የተቀናጀና ወጥ የሆነ አሰራርን በማስፈን ለዜጎች የዘመነ አገልግሎት ለመስጠት ይረዳል ብለዋል። ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተቀናጀ የመረጃ አያያዝ ሥርዓት በመፍጠር የሀገርን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ፣ የመልካም አስተዳደር ጉዳዮችን ጨምሮ ለበርካታ ዘርፎች ጠቀሜታ ያለው መሆኑንም አስረድተዋል። በተቋሙ ምዕራብ የሪጅን ኦፕሬሽን ዳይሬክተር አቶ አስረስ ብረሃኑ እንዳሉት ኢትዮ-ቴሌኮም ከግንኙነት አገልግሎት በተጨማሪ የማህበረሰባችንን የእለት ተእለት ኑሮ ለማቃለል፣ የኢንተርፕራይዝ ስርአቶችን ለማዘመን እና ምርታማነትን ለማሳደግ ሰፋ ያለ ዲጂታል መፍትሄዎችን ለማቅረብ በርካታ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል። በአዳማ በተካሄደው የማስጀመሪያ መርሃ ግብር የኢትዮ ቴሌኮም የደንበኞች አገልግሎት ዋና ኦፊሰር አቶ ተሬሳ በለጠ እንዳሉት ኢትዮ-ቴሌኮም የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ዜጎች በኢኮኖሚ ማህበራዊና ሌሎች አገልግሎቶች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እንዲያገኙ የተጀመረ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተለይም የኦንላይን ግብይትን ምቹ በማድረግ፤ የብድር አገልግሎቶችና የቢሮዎችን የስራ ትስስር በመፍጠር የተሻለ አገልግሎት ማግኘት የሚያስችል መሆኑ ጠቀሜታውን ከፍ ያደርገዋል ብለዋል፡፡ በተመሳሳይ የምዝገባ መርሃ ግብሩ በጋምቤላ ከተማም ተጀምሯል። ኢትዮ ቴሌኮም አዲስ አበባን ጨምሮ በ29 ከተሞች በሚገኙ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላቱ ለዜጎች ብሄራዊ ዲጂታል መታወቂያ ለማቅረብ የምዝገባ፣ የማከፋፈያ እና የማጣራት ስራ በይፋ መጀመሩን አስታውቋል።    
ኢትዮ ቴሌኮም በሀገር አቀፍ ደረጃ የብሄራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባን አስጀመረ
Apr 24, 2024 89
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2016 (ኢዜአ)፡- ኢትዮ ቴሌኮም በሀገር አቀፍ ደረጃ የብሄራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባን አስጀመረ። በምዝገባ ማስጀመሪያ ሥነ ሥርዓቱ ላይ በሀገር አቀፍ ደረጃ እስከ 2018 ዓ.ም ለ90 ሚሊዮን ዜጎች አገልግሎቱን ለመስጠት መታቀዱን እና ኢትዮ ቴሌኮም 32 ሚሊዮን ዜጎችን ተደራሽ ለማድረግ ግብ ማስቀመጡ ተገልጿል። የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አስቻይ ከሆኑ ጉዳዮች አንዱ ተዓማኒነት ያለው የማንነት መለያ ዲጂታል መታወቂያ ነው ብለዋል። ዲጂታል የክፍያ አገልግሎቶችን በቀላሉ ተደራሽ ለማድረግ ወሳኝ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ ሁሉም የድርሻውን መወጣት እንዳለበትም ነው ያስታወቁት። ኢትዮጵያ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን ወደ ስራ መግባቷን አውስተው፥ ብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ አካታች ዲጂታል ኢኮኖሚን ለመገንባትና ዜጎች በኢኮኖሚው ዕኩል ተጠቃሚ እንዲሆኑ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ የዲጂታል ዕድሎችን በመጠቀም ፈጠራ የታከለበትና በዕውቀት ላይ የተመሰረተ ኢኮኖሚ ለመገንባት ወሳኝ እንደሆነም አንስተዋል። የብሔራዊ ዲጅታል መታወቂያ ምዝገባው አዲስ አበባን ጨምሮ በ29 ከተሞች ዛሬ በይፋ የተጀመረ ሲሆን፥ ዜጎች ባሉበት ቦታ ሆነው በቴሌብር ሱፐርአፕ ምዝገባውን ማከናወን እንደሚችሉም ነው የተገለፀው። በቀጣይም አገልግሎቱን የበለጠ ተደራሽ ለማድረግ በተለያዩ ከተሞች የማስፋፊያ ስራ እንደሚሰራ ጠቁመዋል።  
በኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት ጥራትና ዘመናዊነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ሥራዎች ተስፋ ሰጪ ናቸው
Apr 24, 2024 135
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የቴሌኮም አገልግሎት ጥራት፣ ዘመናዊነትንና ተወዳዳሪነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ሥራዎች ተስፋ ሰጪ ናቸው ሲል የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን ገለጸ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የ2016 በጀት ዓመት የመንግሥት የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም በተገመገመበት ወቅት የፌዴራል ተቋማት የሱፐርቪዥን ቡድን ተቋቁሞ ትኩረት በተሰጣቸው ዘርፎች ላይ የመስክ ምልከታ እንዲያደርግ አቅጣጫ ማስቀመጣቸው ይታወሳል። በፕላንና ልማት ሚኒስቴር አስተባባሪነት የሚመራው የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን በኢትዮጵያ ኮሙኒኬሽን ባለሥልጣን ዋና መሥሪያ ቤት ተገኝቶ የሥራ እንቅስቃሴ ተመልክቷል።   የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ባልቻ ሮባ፤ ተቋሙ ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ ዓለም አቀፍ አገልግሎት ሰጪዎች ወደ ኢትዮጵያ ገብተው እንዲሰሩ ፈቃድ በመስጠትና በቁጥጥር ሥራ ያከናወናቸውን ተግባራት አቅርበዋል። የኢትዮጵያ ኮሙኒኬሽን ባለሥልጣን በ2012 ዓ.ም ሥራ በመጀመር የቴሌኮም ዘርፍ ሪፎርሙን ለማሳካት ዘርፈ-ብዙ ሥራዎችን ማከናወኑን ገልፀዋል። በዚህም በኢትዮጵያ አዲስ የቴሌኮም አገልግሎት ሰጪ (ሳፋሪኮም) ገብቶ እንዲሰራ በተደረገው መሠረት የቴሌኮም ዘርፍ በውድድር እንዲሰጥ መሠረት መጣሉን አንስተዋል። ክትትልና ቁጥጥርን ለማጠናከር ከ18 በላይ የሕግ ማዕቀፎችና መመሪያዎችን በማዘጋጀት ሥራ ላይ ማዋሉን ገልፀዋል። በተመሳሳይ ሁሉን አቀፍ የኢንተርኔት ተደራሽነት ክፍተት ጥናት በማድረግና ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራትን ተናግረዋል። ከ28 ሺህ በላይ ልዩ ልዩ የቴሌኮሙኒኬሽን መሳሪያዎችን ብቃት በማረጋገጥ ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ ፈቃድ መስጠቱንም ጨምረዋል። በተለይም የአገልግሎት ጥራትን በመቆጣጠር በኩል በዳታ አገልግሎት፣ በአጭር መልዕክትና በሞባይል ድምፅ በአንድ ጊዜ እስከ ሦስት አገልግሎት ሰጪዎችን ኔትወርክ መለካት የሚያስችል መሳሪያ መኖሩን ጠቅሰዋል። የሰው ኃይል በበቂ ሁኔታ አለመሟላት፣ በአቅም ግንባታና ሌሎች ተቋሙ ሥራዎቹን ለማከናወን ተግዳሮቶች እንደሆኑም ዋና ዳይሬክተሩ አንስተዋል። የኮሚቴው የኮሙኒኬሽን ሱፐርቪዥን ቡድን አስተባባሪ ገብሬ አላምኔ፤ ባለሥልጣኑ የአገሪቱን የቴሌኮም ሥርዓት ከመቆጣጠር ውድድርና ጥራትን ለማረጋገጥ የተገበራቸው ሥራዎች አበረታች መሆናቸውን በሱፐርቪዥን ማረጋገጣቸውን ተናግረዋል።   ከተደራሽነት፣ በሰው ኃይል ማብቃት፣ ለቁጥጥርና ክትትል ሥራ የሚያግዙ መሠረተ-ልማቶችና ዘመናዊ አሠራሮችን መዘርጋቱን መገንዘባቸውን ጨምረዋል። ተቋሙ በአገልግሎት ጥራት፣ እራሱን በማስተዋወቅና በሌሎች ጉዳዮች ከሱፐርቪዥን ቡድኑ የተሰጡትን አስተያየቶች በመተግበር ጠንካራ ተቆጣጣሪ ለመሆን እንደሚሰራ ዋና ዳይሬክተሩ ገልፀዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያን በማሳካት ሂደት ጠንካራ አሠራር ለመዘርጋት በሲምካርድ ምዝገባ ላይ የተጀመሩ ሥራዎች በቀጣይም በትኩረት እንደሚሰራ አንስተዋል። በሱፐርቪዥን ወቅት በተቋሙ ሥራዎችን ለማከናወን የተነሱ ጥያቄዎች ለሚመለከተው አካል እንደሚያቀርቡ ጠቁመዋል።                                        
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ሀገርን ከተለዋዋጭ የሳይበር ጥቃት መመከት የሚያስችል አቅም ገንብቷል-የፌደራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን
Apr 24, 2024 125
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2016 (ኢዜአ)፦የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ተለዋዋጭ የሆኑ የሳይበር ጥቃቶችን በብቃት በመመከት የሀገርን ጥቅም ማስከበር የሚያስችል የተሟላ አቅም መፍጠሩን የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን ገለጸ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የ2016 በጀት ዓመት የመንግሥት የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም በተገመገመበት ወቅት የፌዴራል ተቋማት የሱፐርቪዥን ቡድን ተቋቁሞ ትኩረት በተሰጣቸው ዘርፎች ላይ የመስክ ምልከታ እንዲያደርግ አቅጣጫ ማስቀመጣቸው ይታወሳል። በፕላንና ልማት ሚኒስቴር አስተባባሪነት የሚመራው የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና መሥሪያ ቤት ተገኝቶ የመስክ ምልከታ አድርጓል። የአስተዳደሩ የስራ ኃላፊዎች በመሰረተ ልማት፣ በተቋም አደረጃጀት፣ ተተኪ የሰው ኃይልን በማፍራትና ሌሎች ተቋሙ እያከናወናቸው የሚገኙ ተግባራትን ለሱፐርቪዥን ቡድኑ ገለጻ አድርገዋል። የሱፐርቪዥን ቡድኑ አስተባባሪ ዘሪሁን ከበደ በዚሁ ወቅት ኢትዮጵያ የሳይበር ጥቃትን መከላከል የሚያስችል ሁሉን አቀፍ አቅም እየገነባች መሆኑን በመስክ ምልከታው እንደተረዱ ገልጸዋል። በተለይም ተለዋዋጭ የሆነውን የሳይበር ጥቃት መመከት የሚያስችሉ፣ ዘመኑ የደረሰባቸውን መሰረተ ልማቶች በመዘርጋትና በሰው ኃይል ዘርፍ የተሰሩ ተግባራት የሚበረታቱ መሆኑን አንስተዋል። በተመሳሳይ በስታርት አፕ እንዲሁም የሳይበርና ቴክኖሎጂ ችሎታ ያላቸው ታዳጊዎች ላይ እየተሰራ ያለው ተግባር ለቀጣይ ሀገራዊ ግብ መሳካት መሰረት የሚጥል መሆኑንም ተናግረዋል። አስተዳደሩ በቀጣይም ያሉትን ጥንካሬዎች በማስቀጠል ክፍተቶችን እያረመ ሀገራዊ ተልዕኮውን በአግባቡ እንዲወጣ አሳስበዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳሬክተር ትግስት ሃሚድ በበኩላቸው የሳይበር ጥቃት ሳይፈጸም የመከላከልና ጥቃት ሲያጋጥም ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም መገንባቱን ገልጸዋል። የቁልፍ ተቋማትን ደህንነት ማስጠበቅ፣ ቴክኖሎጂዎችን በአገር ውስጥ የማልማት፣ የስጋት ዳሰሳ መስራትና ሌሎች የሳይበር ደህንነትን ማስጠበቅ የሚያስችሉ ስራዎች ትኩረት እንደተሰጣቸውም አስረድተዋል። እንደዋና ዳሬክተሯ ገለጻ ብሔራዊ ጥቅምን ለማስጠበቅ ቁልፍ በሆኑ ተቋማት ላይ 24 ሰዓት የሳይበር ደህንነትን የማስጠበቅ ተልዕኮ እየተወጣን ነው ብለዋል። ዋና ዳይሬክተሯ አክለውም የሳይበር ጥቃትን የመከላከል ስራ የሁሉንም ተቋማት ጥረትና የህብረተሰቡን የሳይበር ግንዛቤ ማሳደግ የሚፈልግ በመሆኑ ባለድርሻ አካላት አብረው ሊሰሩ እንደሚገባ ጠቁመዋል።   የአስተዳደሩ ምክትል ዋና ዳሬክተር ዳንኤል ጉታ እንዳሉት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሳይበር ምህዳሩ የሚያስተናግደው የጥቃት ዓይነትና መጠን እየጨመረ መጥቷል። ኢትዮጵያም ይህንን ታሳቢ በማድረግ የሳይበር ጥቃትን በአግባቡ ለመመከት በቴክኖሎጂና በሰው ኃይል አስፈላጊውን አደረጃጀት በመገንባት የሁልጊዜም ዝግጁነት መፍጠሩን ገልጸዋል። የፌደራል ተቋማት የሱፐርቪዥን ቡድን በተመረጡና ትኩረት በተሰጣቸው ዘርፎች የሚያደርገው የመስክ ምልክታ እስከ ሚያዚያ 24 ቀን 2016 ዓ.ም የሚቀጥል ይሆናል፡፡          
ለስታርትአፕ የተሰጠው ትኩረት የፈጠራ ስራዎችን ወደ ተግባር ለማስገባት እድል የሚፈጥር ነው
Apr 23, 2024 91
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 15/2016(ኢዜአ)፡- ለስታርትአፕ የተሰጠው ትኩረት የፈጠራ ስራዎችን ወደ ተግባር ለማስገባት እድል እንደሚፈጥር ስታርትአፖች ገለፁ። በሳይንስ ሙዚየም በመታየት ላይ የሚገኘው የስታርትአፕ ኢትዮጵያ አውደ-ርዕይ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ባለሙያዎችን ለቀጣይ ስራ የሚያበረታታ መሆኑን የተለያዩ ሰዎች አስተያየታቸውን ሰጥተውበታል፡፡ ከመጋቢት 30 እስከ ሚያዝያ 20 ቀን 2016 ዓ.ም ለሕዝብ ዕይታ ክፍት በተደረገው አውደ-ርዕይ በመጀመሪያ ደረጃ በምርት ሙከራና ምርት ወደ ገበያ ማቅረብ የጀመሩ ስታርት አፖች እየተሳፉበት ይገኛሉ። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ ስታርት አፖች ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት የፈጠራ ስራዎችን ወደ ተግባር ለማስገባት እድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል።   ከነዚህ መካከል አንዱ የሆነው ያብቃሉ አሰፋ እናቶች የእጅ ስልካቸውን በመጠቀም ባሉበት ቦታ ሆነው ጤንነታቸውን የሚከታተሉበት ቴክኖሎጂ ማበልፀጉን ተናግሯል። ለስታርትአፕ የተሰጠው ትኩረት የፈጠራ ስራዎችን በቀላሉ በማስተዋወቅ ወደ ስራ ለመግባት የሚያስችል የገንዘብ ድጋፍ ለማግኘት አጋዥ መሆኑን ገልጿል። በተጨማሪም ለዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር የተጀመረውን ጥረት ለመደገፍና ኢኮኖሚውን ለማሳደግ የራሱን ሚና እንዲወጣ ያስችላል ሲል ጠቁሟል።   በስታርት አፕ አውደ ርዕይ ፈጠራውን ያቀረበው ቃለአብ ግርማ በበኩሉ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችን ድጋፍ ከሚሹ ወገኖች ጋር ለማገናኘት የሚያስችል ቴክኖሎጂ ማበልፀጉን ገልጿል። ቴክኖሎጂው የመረዳዳትና የመደጋገፍ ባህልን ለማሳደግ እንደሚያግዝ ተናግሯል።   ምርቶችን ለህብረተሰቡ በቀላሉ ለማቅረብ የሚያስችል ኢ-ኮሜርስና ሎጀስቲክን ያካተተ ቴክኖሎጂ መስራቱን የተናገረው ደግሞ በረከት ታደሰ የተባለ የፈጠራ ባለሙያ ነው ። መንግስት ለስታርት አፕ ትኩረት በመስጠት ፖሊሲዎችን በማዘጋጀትና ሌሎች ድጋፎችን በማድረግ ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን ተናግሯል።   በሳይንስና ኢኖቬሽን ሚኒስቴር የኢኖቬሽን ድጋፍ ባለሙያ አቶ ነገደ ይስሃቅ ስታርት አፖች ፈጠራ ስራዎቻቸውን በማስተዋወቅ ወደ ስራ እንዲገቡ ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸውን መሆኑን አስታውቀዋል። ስታርት አፖች ተወዳዳሪነታቸውን በማሳደግ ውጤታማ እንዲሆኑ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ እየተፈጠረላቸው መሆኑን ገልፀዋል።    
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የትራፊክ አደጋን መቀነስ የሚያስችሉ ዲጂታል አሰራሮች በስፋት ተግባራዊ እንዲደረጉ አሳሰበ
Apr 22, 2024 143
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 14/2016 (ኢዜአ)፦የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት የትራፊክ አደጋን መቀነስ የሚያስችሉ ዲጂታል አሰራሮችን ይበልጥ ተደራሽ እንዲያደርግ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሳሰበ፡፡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የከተማ መሰረተልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የመንገድ ደህንነትና ፈንድ አገልግሎት የ2016 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት እቅድ አፈፃፀም የገፅ ለገፅ ግምገማ አካሂዷል። ቋሚ ኮሚቴው አገልግሎቱ የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ ለተሽከርካሪዎች የፍጥነት መገደቢያ ማሰርን ጨምሮ ተሽከርካሪዎች ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን እንዲጠቀሙ ለማድረግ እየሰራ ያለውን ሰራ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል። የአሽከርካሪ ሙያ ስልጠናና ተሽከርካሪ ቴክኒክ ምርመራ የሚሰጡ ተቋማት ላይ ያለው አሰራር በዲጂታል ስርዓት የታገዘ ለማድረግ በትኩረት መስራት እንዳለበትም አሳስቧል። የትራፊክ አደጋ በተደጋጋሚ የሚደርስባቸው ቦታዎችን በመለየት አደጋን ለመከላከል በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባም ነው የተገለፀው። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ሸዊት ሻንካ፤ መረጃ በተገቢው መልኩ መሰብሰቡ የትራፊክ አደጋን ለመከላከልና አስፈላጊ ህጎችን ለመተግበር የሚያስችል በመሆኑ አገልግሎቱ የመረጃ አያያዝ ስርዓቱን እንዲያዘምን አስገንዝበዋል፡፡ ተቋሙ በመንገድ ትራፊክ አደጋ ዙሪያ ያካሄዳቸው የንቅናቄና ግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ገልፀዋል። በትምህርት ቤቶች ባሉ ክበባት ተማሪዎች የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው እየተሰራ ያለው ስራም ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ተናግረዋል። የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈፃሚ ጀማል አባሶ በበኩላቸው አገልግሎቱ የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ እያከናወነ ካለው ስራ በተጨማሪ የተለያዩ ማሻሻያዎችን እየተገበረ ነው ብለዋል። የተለያዩ ህግና ደንብ፣ ስታንዳርዶችንና መመሪያ ማሻሻያ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው፤ ዲጂታል አሰራርን ተግባራዊ ማድረግ ላይም ትኩረት ተሰጥቷል ነው ያሉት፡፡ የተሽከርካሪ ምርመራ ተቋማትና የፍጥነት መገደቢያ አገጣጠምና አገልግሎቱን ከማዕከል ለመከታተል የሚያስችል ሶፍትዌር እየለማ መሆኑንም ጠቁመዋል። ከተለያዩ ክልሎች የተውጣጡ ባለሙያዎች የተሳተፉበት ዘመቻ በማድረግ በተሽከርካሪና አሽከርካሪዎቸ ላይ ቁጥጥርና ክትትል መደረጉንም ተናግረዋል። በድግግሞሽ ከ9 ነጥብ 8 ሚሊዮን በላይ ተሽከርካሪዎች ላይ በመደበኛ፣ ድንገተኛና የቴክኒክ ቁጥጥር መደረጉን ጠቅሰው፤ ጉድለት በተገኘባቸው 2 ሚሊዮን በላይ ተሽከርካሪዎች ላይ ቅጣት መተላለፉን ጠቁመዋል፡፡ በዚህም በተያዘው በጀት ዓመት ስድስት ወራት በትራፊክ አደጋ የተመዘገበው ሞት ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በ514 መቀነሱን ተናግረዋል። የአካል ጉዳት ደግሞ በ216 መቀነሱን ጠቁመዋል፡፡ ከመንጃ ፍቃድ አሰጣጥና ተሽከርካሪ ምርመራ ጋር የሚነሱ ችግሮችን ለመፍታት የተሽከርካሪ ምርመራን በኦንላይን መከታተል የሚያስችል ስርዓት ለመዘርጋት እየተሰራ ነው ያሉት ደግሞ የአገልግሎቱ ምክትል ስራ አስፈፃሚ ፈቲያ ደድገባ ናቸው። የመንጃ ፍቃድ አሰጣጡን ለማዘመን ከሰነድ ክለሳ ጀምሮ እየተሰራ መሆኑም ተጠቁሟል። የመረጃ ተዓማኒነት እንዲኖር ለማስቻልም የትራፊክ አደጋ ምዝገባን በሲስተም ለመመዝገብ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።  
ብሄራዊ የዲጂታል መታወቂያ ስርአት ወጥ የሆነ ቀልጣፋና የተቀናጀ  አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል ነው
Apr 21, 2024 178
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 13 /2016(ኢዜአ) ፡ ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ) ወጥ የሆነ ሀገራዊ የመረጃ አያያዝ ሥርዓት በመዘርጋት የተቀናጀ፣ ቀልጣፋና የተረጋገጠ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል መሆኑን የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት አስታወቀ። የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ሥርዓት ማለት መሠረታዊ የሆኑ የግል ዲሞግራፊክ እና ተፈጥሯዊ የሆነውን የዓይን፣ የጣትና የፊት የባዮሜትሪክ መረጃዎችን መዝግቦ በመያዝ በማዕከላዊ ቋት የሚያስቀምጥ አሠራር ነው። የዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ከተከናወነ በኋላ ልዩ ቁጥር በመስጠት ተመዝጋቢው የተደራጀና አስተማማኝ የዲጂታል መታወቂያ እንዲኖረውም ያደርጋል። የዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት ለሰላምና ደኅንነት፣ ለተፋጠነ ልማት፣ የምጣኔ ኃብት ሽግግርና መልካም አስተዳደር የላቀ ጠቀሜታ እንዳለው ይታወቃል። የፖሊሲ ቀረፃን፣ የምጣኔ ኃብትና ማኅበራዊ ልማት ክንውንን አካታች ለማድረግም እንዲሁ። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሐሚድ ኪኒሶ፤ የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ) ወቅቱን የዋጀ ለሀገርና ሕዝብ የሚጠቅም ዘመናዊ የአሠራር ሥርዓት መሆኑን ገልፀዋል። በኢትዮጵያ አንድ ወጥ የሆነ የመረጃ አያያዝ ሥርዓት በመዘርጋት የተቀናጀ፣ ቀልጣፋና የተረጋገጠ አገልግሎት ለመስጠት የላቀ ጠቀሜታ የሚኖረው መሆኑን ተናግረዋል። የውል ስምምነቶችና ሌሎችንም ሰነዶች በማጣራት በቴክኖሎጂ የታገዘ ምዝገባና ማረጋገጫ የሚደረግበት ዘመናዊ አሠራር መሆኑንም ጠቅሰዋል። የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት በ15 ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቱ በየቀኑ በአማካይ ለ6 ሺህ 500 ሰዎች አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል ብለዋል። ከዚህ ቀደም ከመታወቂያ ጋር በተያያዘ ችግሮች እንደነበሩ አስታውሰው፤ የዲጂታል መታወቂያ ተግባራዊ ከሆነ በኋላ ግን ጥራት ያለው ቀልጣፋና የተቀናጀ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ገልፀዋል። የዲጂታል መታወቂያ ለተቋሙ አገልግሎት መሳለጥ ወሳኝ በመሆኑ ተቋማቸው ከብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ (ፋይዳ) ጽህፈት ቤት ጋር በመቀናጀት እየመዘገበ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህም እስካሁን ከ70 ሺህ 300 በላይ ተገልጋዮችን ለብሄራዊ መታወቂያ መመዝገብ ችለናል ሲሉ ተናግረዋል።          
አለም አቀፉ የታዳሽ ሀይል ኤጀንሲ ኢትዮጵያ የቀጣናው ሀገራትን በታዳሽ ሀይል ለማስተሳሰር የምታደርገውን ጥረት አደነቀ
Apr 21, 2024 166
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 13/2016(ኢዜአ)፡- አለም አቀፉ የታዳሽ ሀይል ኤጀንሲ ኢትዮጵያ የቀጣናው ሀገራትን በታዳሽ ሀይል ለማስተሳሰር የምታደርገውን ጥረት አድንቋል። አራተኛ አለም አቀፍ የታዳሽ ሀይል ኤጀንሲ ጉባኤ በአቡ ዳቢ ከተማ ተካሄዷል። በጉባኤው ላይ የውሀና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) እና በኢትዮጵያ በአረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ኡማር ሁሴን ተሳትፈዋል።   በጉባኤው አራተኛ ቀናት ታዳሽ ሀይል ማከማቸት በሚቻልበትና በአፍሪካ የሀይል አቅርቦት ሽግግርን፣ ታዳሽ ሀይልን ማስፋት በሚቻልባቸው ጉዳዮዎችና የዘርፉን የፖሊሲ ማእቀፎች ላይ ምክክር ተደርጓል። እአአ በ2030 አባል ሀገራት ታዳሽ ሀይልን ጥቅም ላይ ለማዋል በጋራ የሚሰሩበትን አቅም ማጉላት የሚቻልበትን ሁኔታን ማጠናከርም የውይይቱ አካል እንደነበር ተገልጿል። በምክክሩ ላይ የውሀና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) እንዳሉት ኢትዮጵያ ታዳሽ ሀይልን ለማበረታታት የመንግስትና የግል አጋርነት ፖሊሲን በመተግበር በጸሀይ ሀይል፣ በንፋስና በእንፋሎት ሀይል የሚሰሩ ፕሮጀክቶችን መተግበሯን አንስተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተቀየሰው የታዳሽ የሀይል ስትራቴጂም በአፍሪካ በ2030 የሀይል አቅርቦትን ተደራሽ ለማድረግ የተጣለውን ግብ ሙሉ በሙሉ ለማሳካት መቃረቧን ጠቁመዋል። በዚህም መንግስት የቀጣናውን ሀገራት በሀይል አቅርቦት ለማስተሳሰር ለኬንያ ፣ለጅቡቲና ለሌሎች ሀገራት ሀይል ማቅረቡን ሲያስታውሱ ይህም ከሀይል አቅርቦት ባለፈ ለቀጣናው ሰላምና መረጋጋት መስፈን ትልቅ አቅም ማበርከቱን ተናግረዋል።   የአለም አቀፉ የታዳሽ ሀይሎች ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አልፋሮ ፔሊኮ በበኩላቸው ለታዳሽ ሀይል የሚመደቡ በጀትን ማሳደግና እንዲሁም የመንግስትና የግል አጋርነትን በማረጋገጥ በቅንጅት መስራት እንዳለበት ሲያነሱ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን አብርክቶ አድንቀዋል። በታዳሽ ሀይል አቅርቦት አሁን ላይ ያልውን 13 ነጥብ 7 ሚሊዮን የስራ እድል ፈጠራ በ2050 ወደ 40 ሚሊዮን ማሳደግ ይገባልም ነው ያሉት። ዘርፉን ለማበረታታትም ሀገራት የፖሊሲ ማሻሻያዎች በታክስ ቅነሳ ፤በድጎማ፣ በዋስትና እና በጥናቶች መደገፍ እንደሚገባቸው መናገራቸውን ከውሀና ኢነርጂ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
ሴቶች በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላቸውን ተሰጥኦ እንዲያወጡ ሊታገዙና ሊበረታቱ  ይገባል- በስታርት አፕ አውደርዕይ የተሳተፉ ሴቶች 
Apr 20, 2024 157
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2016(ኢዜአ)፦ ሴቶች በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላቸውን ተሰጥኦ እንዲያወጡና አገርን የሚጠቅም ተግባራቸውን እንዲያጎለብቱ ሊታገዙና ሊበረታቱ ይገባል ሲሉ በስታርት አፕ አውደርዕይ የተሳተፉ ሴቶች ገለፁ። በ21ኛው ክፍለ ዘመንም ይሁን ወደፊት በእጅ የሚሰሩ ሥራዎች ቁጥርና በየቢሮው በስፋት የሚታዩ የወረቀት ብዛቶች በሙሉ በዘመናዊ፣ በአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች እንደሚቀየሩ የሚያሳዩ ምልክቶች ብዙ ናቸው። በአገራችንም ይህንን ታሳቢ ያደረገ የሳይንስና የፈጠራ ስራዎች እየተበረታቱና ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራባቸው መሆኑ በግልጽ ይታወቃል። በአገሪቱ ያለውን እምቅ የቴክኖሎጂ አቅም ለማስተዋወቅ ከመጋቢት 30 እስከ ሚያዝያ 20 ቀን 2016 ዓ.ም የሚቆየው የኢትዮጵያ "ስታርት አፕ" አውደ-ርዕይ በአዲስ አበባ ተከፍቷል። በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርት፣ በኢንዱስትሪ፣ በፋይናንስና በሌሎች ዘርፍ የተሰማሩ ጀማሪ ሥራ ፈጣሪዎች ''ስታርት አፖች'' በአውደ-ርዕዩ በመሳተፍ ላይ ናቸው። የቢፍሮል ቲዩብ መስራች ሀይከል አህመድ በአውደርዕዩ ተማሪዎች በተግባር የተደገፈ ትምህርት እንዲያገኙ የሚያግዙ ትምህርታዊ ቪዲዮዎችን የሚያቀርብ አማራጭ ይዘው እንደቀረቡ ተናግራለች። እነዚህ ቪዲዮዎች ተማሪዎች ትምህርትን ከንድፈ ሃሳብ በዘለለ በተግባር በመማር ብቁ እንዲሆኑ የሚያግዙ መሆናቸውን ጠቅሳለች። አኪል የተሰኘ አገርበቀል በጎ አድራጎት ድርጅትና በጎ ፍቃደኞችን የሚያገናኝ ድረገፅ ያለማችው ቦንቱ ፉፋ በበኩሏ ድረገፁ በጎ ፍቃደኞችንና በጎ ስራን በማገናኘት በጉልበት፣ ገንዘብና ባላቸው አቅም እንዲደግፉ የሚያስችል ነው ብላለች። በአሁኑ ወቅት በቴክኖሎጂው ዘርፍ የወንዶች የበላይነት ቢስተዋልም በኢትዮጵያ ፈርቀዳጅ ሆነው በዘርፉ የወጡ ሴቶች መኖራቸውን አስተያየት ሰጪዎቹ ጠቅሰዋል። ማንኛዋም ሴት እንደምትችል ካመነች ያለችውን ማድረግ ስለምትችል ስራ ላይ በማተኮር በቴክኖሎጂ ዘርፍ መሰማራት እንደምትችልም ነው የገለፁት። መንግስት እንደዚህ አይነት አውደ ርዕይ አዘጋጅቶ የሚሰሩትን ስራ እንዲያስተዋውቁ፣ ሌሎች የፈጠራ ስራዎችን አይተው እንዲበረታቱና እውቀት እንዲገበዩ በማድረጉ መደሰታቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም እንደዚህ አይነት ራሳቸውን የሚያስተዋውቁበት መድረክ ማዘጋጀትና ያላቸውን እምቅ አቅም አውጥተው ለህዝብ እንዲያሳዩ የማድረጉ ስራ ሊጠናከር ይገባል ሲሉም ተናግረዋል። ከመጋቢት 30 እስከ ሚያዝያ 20 ቀን 2016 ዓ.ም የሚቆየው የኢትዮጵያ "ስታርት አፕ" አውደ-ርዕይ የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በሳይንስ ሙዚየም ለጎብኚዎች ክፍት ተደርጓል።  
ባለመላዎቹ ታዳጊዎች
Apr 19, 2024 267
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ ችግርን ወደ እድል የቀየሩ ባለመላዎቹ ታዳጊዎች ከመጋቢት 30 እስከ ሚያዝያ 20 ቀን 2016 ዓ.ም የሚቆየው የኢትዮጵያ "ስታርት አፕ" አውደ-ርዕይ የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በሳይንስ ሙዚየም ለጎብኚዎች ክፍት ተደርጓል። በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርት፣ በኢንዱስትሪ፣ በፋይናንስና በሌሎች ዘርፍ የተሰማሩ ጀማሪ ሥራ ፈጣሪዎች ''ስታርት አፖች'' በአውደ-ርዕዩ በመሳተፍ ላይ ናቸው። አውደ-ርዕዩ የተዘጋጀው በአገሪቱ የሚገኙ ስታርት አፖች ያላቸውን ምርትና አገልግሎት እንዲሁም ፈጠራዎች ተደራሽ ለማድረግ ነው። የአቤም ዩዝ አካዳሚ የሰባተኛ ክፍል ተማሪ የሆኑት ጎዶሊያስ ሙሉጌታና ሰላዲን መራዊ የግለሰብ መረጃን ወይንም ሲቪ የሚያደራጅ ድረ-ገፅ ሰርተው በስታርት አፕ አውደ-ርዕይ አቅርበዋል።   የታዳጊ ጎዶሊያስ ወንድም ስራ ለማመልከት ሲወጣ ''ሲቪ'' ረስቶ ወደቤት በመመለስ ለተጨማሪ ወጪና እንግልት መዳረጉ የዚህ ድረ-ገፅ መልማት መነሻ የሆነ ምክንያት ነው። ሰዎች ስራን ለመቀጠር የሚያስገቡት የራስ መግለጫ ''ሲቪ'' በእጅ ስልካቸው ኖሮ በማንኛውም ሰዓት ለሚፈልጉት ቀጣሪ ማስገባት የሚያስችል ድረ-ገፅ የሰሩት ታዳጊዎች የአይ ሲ ቲ መምህራቸው ለዚህ ስራቸው እገዛ እንዳደረገላቸው ተናግረዋል። ድረ-ገፁ ስለግለሰቡ የትምህርት ደረጃን ጨምሮ፣ አድራሻ፣ ክህሎቶችና የሰዎችን ምስክርነትን ማካተት የሚቻልበት መሆኑን ተናግረዋል። ድረ-ገፁ የሰዎችን ብቻ ሳይሆን የድርጅቶችን መረጃ እንዲያስቀምጥ ተደርጎ የተዘጋጀ መሆኑንም ታዳጊዎቹ ያስረዳሉ። በሳይንስ ሙዚየም የተዘጋጀው አውደርዕይ ላይ መሳተፋቸው ከሌሎች ስታርት አፖች ልምድ እንዲቀስሙና እውቀታቸውን እንዲያዳብሩ እድል የሚፈጥርላቸው መሆኑንም ገልፀዋል። ስራቸውን እንዲያሳዩ እድል ስለተፈጠረላቸውና እዚህ ደረጃ ላይ እንዲደርሱ እገዛ ላደረጉላቸው አካላትም ምስጋና አቅርበዋል። በቀጣይም ችግር ፈቺ የምርመር ስራዎችን በመስራት አገራቸውን ለመጥቀም እንደሚሰሩ ገልጸዋል።  
ኢትዮጵያ ለስታርት አፕ የሰጠችው ትኩረት የዲጅታል ኢኮኖሚ ግንባታ ርዕይና ተስፋዋን የሚያሳካ ነው- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 19, 2024 203
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለስታርት አፕ የሰጠችው ትኩረት የዲጅታል ኢኮኖሚ ግንባታ ርዕይና ተስፋዋን የሚያሳካ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በሳይንስ ሙዚየም የተከፈተውን የስታርት አፕ ኢትዮጵያ አውደ ርዕይ ጎብኝተዋል።   በጉብኝታቸውም ኢትዮጵያን በብዙ መልኩ የሚጠቅሙ ችግር ፈቺ የፈጠራ ሀሳቦችን መመልከታቸውን ተናግረዋል። ሀገርን ሊያሳድጉ የሚችሉ የፈጠራ ሀሳቦች ያሏቸው ወጣቶችና ታዳጊዎችን የኢትዮጵያ እድገት ተስፋዎች መሆናቸውን ጠቅሰው፤ መንግስት ይህንን በመገንዘብ ለዘርፉ ልዩ ትኩረት መስጠቱን አንስተዋል።   10 ዓመቱ የልማት እቅድ የገቢና ወጪ ምርቶችን ለማመጣጠንና የቴክኖሎጂ ፈጠራን ለማሳደግ የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ለማሳካት ስታርት አፖች ሚናቸው ትልቅ ነው ብለዋል። መንግስት ስታርት አፖችን ለማጠናከር እየሰራ ስለመሆኑ አንስተው፤ ለአብነትም ምርቶቻቸውን ገዝቶ መጠቀምን የሚያበረታታ እንዲሁም የፋይናንስ ድጋፍ እንዲያገኙ የሚያደርጉ የፖሊሲ አቅጣጫዎችንና የህግ ማዕቀፎችን ወደ ስራ ማስገባቱን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂና በዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ብዙ ተስፋ እንዳላት ገልጸው፥ ኢትዮ ቴሌኮም አካታች የዲጅታል ኢኮኖሚ ስርዓትን በማሳለጥ ትላልቅ ስራዎችን እያከናወነ ነው ብለዋል። በተለይ በቴሌ ብር አገልግሎት አነስተኛ ብድሮችን በማቅረብ እና አርሶና አርብቶ አደሩን ጭምር የሚያሳትፉ ማዕቀፎችን በመተግበር ትልቅ እምርታ እያስመዘገበ እንደሆነ ጠቅሰዋል። በሰው ሰራሽ አስተውሎትና በቴክኖሎጂ ፈጠራ ያሉ ጅምሮች ኢትዮጵያ ያላትን ግዙፍ ራዕይ ማሳካት እንደሚቻል የሚያሳዩ መሆናቸውን አስረድተዋል። የመንግስት አገልግሎትን ለማዘመን ትልቅ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸው፤ በተለይም ቴክኖሎጅን ያወቀና የአገልጋይነት መንፈስ ያለው የሰው ኃይል ለመገንባት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል ኢትዮጵያ በቀጣናው ብሎም በአፍሪካ የዲጅታል ኢኮኖሚ ማዕከል ለመሆን እየሰራች መሆኑንም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡ ሀገራዊ የብልፅግና ጉዞን ለማሳካት በየክልሎች ያሉ ስታርት አፖችን ሁሉም ሊያበረታታ እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡            
የግሉ ዘርፍ በዲጂታል ምህዳሩ ላይ ያለውን ተሳትፎ በማጎልበት ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ነው- የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር
Apr 19, 2024 125
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 11/2016 (ኢዜአ)፦የግሉ ሴክተር በዲጂታል ምህዳሩ ላይ ያለውን ተሳትፎ በማጎልበት ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን ዓለማየሁ ገለፁ። ራይድ ትራንስፖርት እና ታዋቂው ዓለም አቀፍ የዲጂታል ክፍያ ተቋም ቪዛ በኢትዮጵያ የትራንስፖርት ክፍያን ለማቀላጠፍ የሚያስችል ጥምረት መፍጠራቸውን አስታወቀዋል። ጥምረቱ በኢትዮጵያ የሚኖሩ የውጭ አገር ዜጎች እና ዳያስፖራዎች የቪዛ ካርዳቸውን ብቻ በመጠቀም የትራንስፖርት ክፍያቸውን እንዲያከናውኑ የሚያስችል ነው፡፡ ይህም ጎብኚዎች አስተማማኝና ቀልጣፋ ትራንስፖርት በማግኘት በኢትዮጵያ አስደሳች ቆይታ እንዲኖራቸው የሚያደርግ ነው ተብሏል፡፡ በመድረኩ የተገኙት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን አለማየሁ “ዲጂታል ኢትዮጵያ”ን እውን ለማድረግ ከሚከናወኑ ስራዎች መካከል ዲጂታል ክፍያ አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የዲጂታል ክፍያ ስርዓትም የተቀላጠፈና ዘመናዊ አሰራር ተደራሽ ለማድረግ እንደሚያግዝ ነው ያብራሩት፡፡ ለዲጂታል ኢትዮጵያ ግንባታ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከዚህ አኳያ መንግስት የዲጂታል ምህዳሩን ምቹ ማድረግ ጨምሮ የሚጠበቅበትን ድጋፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡ የሃይብሪድ ዲዛይንስ እና ራይድ መስራች ሳምራዊት ፍቅሩ፤ ጥምረቱ "ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025" እውን ለማድረግ እየተከናወነ ካለው ስራ ጋር የሚጣጣም መሆኑን ጠቁመዋል፡፡   ጥምረቱ ኢትዮጵያን የሚጎበኙ ቱሪስቶች ጥሬ ገንዘብ ሳይጠቀሙ በቪዛ ካርዳቸው ብቻ አገልግሎት እንዲያገኙ እንደሚያደርግም ነው የተናገሩት፡፡ በኢትዮጵያ የቪዛ ዳይሬክተር ያሬድ እንዳለ በበኩላቸው፤ ቪዛ የተቀላጠፈ እና አስተማማኝ የዲጂታል ክፍያን ለሁሉም እና በሁሉም ቦታ ለማዳረስ እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   በመሆኑም ከራይድ ጋር የተጀመረው ጥምረት የኢትዮጵያን የጉዞ እና ቱሪዝም ዘርፍ ለማዘመን ሚናው የጎላ ነው ብለዋል፡፡ በቀጣይም የቪዛ ክፍያ ስርዓትን በሌሎች አገልግሎቶችም ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ እንደሚሰራም ነው የገለጹት፡፡  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም