ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
የዩኒቨርሲቲ - ኢንዱስትሪ ትስስር የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግርን ያጎለብታል - ምሁራን
Oct 20, 2025 114
ሐረማያ፤ ጥቅምት 10/2018(ኢዜአ)፦ የዩኒቨርሲቲ - ኢንዱስትሪ ትስስር የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር እንዲጎለብት በማድረግ ከፍተኛ ጠቀሜታ የሚያበረክት መሆኑን ምሁራን ገለጹ። የምስራቅ ኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲ-ኢንዱስትሪ ትስስር ፎረም ምስረታ በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ተካሂዷል። በምክክሩ መድረክ ላይ የተሳተፉት ምሁራን ለኢዜአ እንደተናገሩት የዩኒቨርሲቲ - ኢንዱስትሪ ትስስር የምርምር ቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር እንዲጎለብት ፋይዳው የላቀ ነው። በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂ ሽግግርና ኢንዱስትሪ ትስስር አስተባባሪ ፈይሳ ሁንዴሳ እንዳሉት፤ ትስስሩ ከዚህ ቀደም ዩኒቨርሲቲዎችና - ኢንዱስትሪዎች በተበጣጠሰ መንገድ የሚያከናውኑት ስራዎችን ወጥ እንዲሆን የሚያስችል ነው። ትስስሩም የዩኒቨርsiቲ ተማሪዎች በንድፈ ሀሳብ የቀሰሙትን እውቀት በኢንዱስትሪዎች የተግባር ልምምድ እንዲያገኙ የሚያስችል ነው ብለዋል። ትስስሩ ኢንዱስትሪዎች የሚያጋጥማቸውን ችግሮች ለመፍታት ከዩኒቨርሲቲዎች ስልጠና፣ ማማከርና የምርምር ቴክኖሎጂ ውጤቶችን እንዲያገኙ ያስችላል ያሉት ደግሞ በድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የኢንዱስትሪ ትስስርና የቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክተር እሸቱ መኮንን(ዶ/ር) ናቸው። በኦዳ ቡልቱ ዩኒቨርሲቲ የምርምር፣ ዓለም አቀፍ ግንኙነት እና አጋርነት ዳይሬክተር ጥምቀተ ዳኜ(ዶ/ር) በበኩላቸው የዩኒቨርሲቲ - ኢንዱስትሪ ትስስር ሀገራዊ የልማት እቅዶችን በጋራ ለማሳካት እገዛ ያደርጋል። እንዲሁም የማህበረሰብ ችግሮችን በቅርበት ለመፍታትና የጋራ ችግሮችን አቅዶ በጋራ ለመቅረፍ ብሎም መፍትሄ ለማምጣት ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን አክለዋል። ትስስሩ ዩኒቨርሲቲዎችን ከኢንዱስትሪዎች ጋር በማስተሳሰር በተግባርና ንድፈ-ሃሳብ የዳበረ የሰው ሃይል ለማፍራት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋል ያሉት ደግሞ የድሬዳዋ ነጻ ንግድ ቀጣና ዋና ስራ አስኪያጅ አህመድ ረሺድ ናቸው። በፎረም ምስረታው የምክክር መድረክ ላይ የሐረማያ፣ ድሬዳዋ፣ ሰመራ፣ ጅግጅጋ፣ ኦዳቡልቱምና ቀብሪደሃር ዩኒቨርሲቲዎች፣ የትምህርት ሞያ ስልጠና ኮሌጆች እንዲሁም በአካባቢው የሚገኙ የመንግስት እና የግል ኢንዱስትሪ ተወካዮች ተገኝተዋል።
ስታርት አፕ ለስራ እድል ፈጠራ እድገት የሚኖረውን አቅም ለመጠቀም ምቹ መደላድል እየተፈጠረ ነው
Oct 19, 2025 194
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 9/2018 (ኢዜአ)፡-ስታርት አፕ ለስራ እድል ፈጠራ እድገት የሚኖረውን አቅም ለመጠቀም ምቹ መደላድል እየተፈጠረ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ገለፁ። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የስታርት አፕ ስነ ምኅዳሩን ማስፋት የሚያስችል የክህሎት ልማት እና አዳዲስ የስራ ዕድል ፈጠራን የሚያበረታቱ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው፡፡ አዳዲስ የፈጠራ ሃሳብ ያላቸው ወጣቶች የሚወዳደሩበት "ብሩህ ኢትዮጵያ" የክህሎት ውድድር ሀገራዊ ልማትን የሚያሳልጥና ስታርት አፖችን ማፍራት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ባለፉት አራት ዓመታት በሀገር አቀፍ ደረጃ 1 ሺህ 350 የፈጠራ ሀሳብ ላላቸው ዜጎች እውቅና ተሰጥቷል ብለዋል፡፡ በሀገሪቱ የሚኖረውን ፋይዳ አሟጦ ለመጠቀም አዳዲስ የፈጠራ ሀሳብ ላላቸው ስታርት አፖች የመስሪያ ቦታ፣ የፋይናንስ፣ የአቅም ግንባታና ሌሎች ድጋፎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል፡፡ የዜጎችን የስራ እድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት ስታርት አፕ ወሳኝ መሆኑን በማንሳት፤ ስታርት አፖች ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ገልጸዋል፡፡ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የስታርት አፕ ዘርፍ ኃላፊ ሙልጌታ ውቤ በበኩላቸው፤የወጣቶች የስራ ፈጠራ ዝንባሌ እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡ መንግስት የወጣቶችን ተሳተፎ ለማሳደግና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የስታርት አፕ አዋጅ በማጽደቅ ወደ ሥራ ገብቷል ብለዋል፡፡ የፈጠራ ሀሳቦች ስታርት አፕ መሆናቸው በህግ ተለይቶ ምዝገባና ስያሜ ከተሰጠ በኋላ አስፈላጊው የፋይናንስና ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞችን እንዲያገኙ እንደሚደረግ ገልጸዋል፡፡ አዋጁን ገቢራዊ ለማድረግ ሀገር አቀፍ የስታርት አፕ ፖርታል እየተዘጋጀ መሆኑን ገልጸው፤ የማስፈጸሚያ ደንቦችና መመሪያዎች ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በሸገር ከተማ ለተገልጋዮች ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Oct 18, 2025 154
ሸገር፤ ጥቅምት 8/2018(ኢዜአ)፦ በሸገር ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እንግልትን በማስቀረት ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ተገልጋዮች ተናገሩ። በሸገር ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከተጀመረ ወዲህ ከተመዘገቡት ከ11ሺህ 224 ተገልጋዮች አብዛኞቹ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘታቸውን እንደገለጹም ተመላክቷል። ከተጠቃሚዎቹ መካከል በአስተዳደሩ የፉሪ ክፍለ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ሁዳ አብዱልከሪም፤ በአሁኑ ወቅት በማዕከሉ እያገኙት ያለው አገልግሎት በእጅጉ መሻሻሉን ለኢዜአ ተናግረዋል። ከዚህ በፊት አገልግሎት ለማግኘት ውጣ ውረድ ብሎም ላልተገባ ወጪ ሲዳረጉ እንደነበር አውስተው፤ አሁን ላይ በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚፈልጉትን አገልግሎት በማግኘት ምቹ ሁኔታ አንደተፈጠረላቸው ገልጸዋል። ቀደም ሲል በነበረው አገልግሎት ፋይል የመጥፋት አጋጣሚና ሌሎችም ችግሮች እንደነበር በማስታወስ አስተያየት የሰጡት ደግሞ ከገላን ክፍለ ከተማ የመጡ አቶ ወርቅነህ በንቲ ናቸው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ አገልግሎት ሰጪ ባለሙያዎቹ መልካም ስነምግባር በመላበስ ከአስር ደቂቃ በታች ግልጽና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት እንደሚያስተናግዱና በዚህም መደሰታቸውን ተናግረዋል። ሌላው ተገልጋይ ከኩራጅዳ ክፍለ ከተማ የመጡት አቶ ሀብታሙ ጆቴ፤ በከተማው የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከተጀመረ ወዲህ ከ15 ደቂቃ ባነሰ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እያገኙ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። የሸገር ከተማ አስተዳደር የአንድ ማዕከል አገልግሎት ኦፕሬሽን ዘርፍ አስተባባሪ አቶ ካሳሁን ጆብር እንዳሉት፤ ቀደም ሲል በከተማው የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት በተበታተነና በተራራቀ መልኩ የሚያካሄዱት አሰራር በቴክኖሎጂ ያልተደገፈና የመረጃ ስርዓቱ ያልተሟላ ነበረ ። አገልግሎቱን ለማሻሻል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በማስጀመር የሚያስፈልጉትን ቴክኖሎጂና የሰው ሃይል በማሟላት ለማሕበረሰቡ ተደራሽ፤ ቀልጣፋና ፈጣን አገልግሎት እየተሰጠ ነው ብለዋል። ይህ አሰራር ከተጀመረ በሶስት ወራት ውስጥም ከተመዘገቡት ከ11ሺ224 ሰዎች ውስጥ አስር ሺህ ሰዎች አገልግሎት ማግኘት መቻላቸውን ጠቅሰዋል። በቀጣይ አገልግሎቱን የበለጠ በማስፋፋት ለሁሉም ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸው፤ ለባለሙያው የሚሰጠው የአቅም ግንባታ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ተገልጋዮች የሚጠበቅባቸውን አሟልተው እንዲገኙ ግንዛቤ ከመስጠት ጎን ለጎን በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር መመቻቸቱን አስረድተዋል። በኦሮሚያ ክልል ደረጃ ከሸገር ከተማ በተጨማሪ በቢሾፍቱ፤ አዳማ፤ ሻሸመኔና ጅማ ከተሞች መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መጀመሩ የሚታወስ ነው።
የልህቀት ማዕከሉ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም የሚቆም ሚዲያ እና ሙያዊ ሥነ ምግባርን የተላበሰ ጋዜጠኛ ለመፍጠር ያስችላል
Oct 18, 2025 193
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 8/2018 (ኢዜአ)፡- የሚዲያ ልህቀት ማዕከል ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም የሚቆም ሚዲያ እና ሙያዊ ሥነ ምግባርን የተላበሰ ጋዜጠኛ ለመፍጠር የሚያስችል መሆኑን የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሳምሶን መኮንን (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የመገናኛ ብዙኃን ለሀገር ግንባታ፣ ለዜጎች የመረጃ ተደራሽነትና ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ጉልህ ሚና እንዲኖረው የዓለምን ነባረዊ ሁኔታ የዋጀ የዘርፉ ባለሙያ እና ቴክኖሎጂ መታጠቅ አለባቸው፡፡ በኢትዮጵያ ከለውጡ በኋላ የመገናኛ ብዙኃንና ጋዜጠኞች ዘርፉ የሚጠይቀውን ሙያዊ ሥነ ምግባር ተላብሰው ለሀገር ግንባታና ለዜጎች ተደራሽነት በነፃነት መስራት የሚችሉባቸው የህግና የአሰራር ማሻሻያዎች ተደርገዋል፡፡ በቅርቡም የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎችን ዕውቀትና ክህሎት በምርምር፣ በማማከርና ስልጠና ማሳደግ የሚያስችል የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል ሥራ ጀምሯል፡፡ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሳምሶን መኮንን (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ አዲስ አበባን ጨምሮ በ25 ዩኒቨርሲቲዎች የጋዜጠኝነት ትምህርት እየተሰጠ ነው፡፡ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትምህርቱን መስጠታቸው ትልቅ ነገር መሆኑን ያወሱት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ሆኖም አብዛኞቹ የጋዜጠኝነት ምሩቃን የንድፈ ሃሳብ እንጂ የተግባር ዕውቀትና ክህሎት እንደሚጎድላቸው ለይተናል ብለዋል፡፡ ጋዜጠኝነት ጽንሰ ሀሳቡን ተረድቶ ትንታኔ መስጠትና ማብራራት ቢሆንም ክፍተት ይታያል ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ በሥራ ላይ ያሉ ጋዜጠኞች ተለዋዋጭ ከሆነው የዓለም ነባራዊ ሁኔታ ጋር በየጊዜው መዘመን እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ሲሰጥ የቆየው ስልጠና ውስን ዓላማን ብቻ ለማስፈፀም እንደነበር ገልጸው፤ ኢትዮጵያ ምን ዓይነት ጋዜጠኝነት ትፈልጋለች የሚለውን መመለስ የሚያስችል የተቀናጀ ስልጠና አልነበረም ብለዋል፡፡ ጋዜጠኝነት ከዓለም ነባራዊ አውድ ጋር የተጣጣመ ቀጣይነት ያለው ዝማኔ ይፈልጋል ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የኢትዮጵያ የሚዲያ ልህቀት ማዕከልን ማቋቋም ማስፈለጉን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ኢትዮጵያን የሚመስል ዘመኑን የዋጀ የመገናኛ ብዙኃንና የጋዜጠኝነት ሙያ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል ግቡ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅምና ለሀገር ግንባታ የሚቆም፣ ለዜጎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚተጋ የመገናኛ ብዙኃንና ጋዜጠኛ ማፍራት መሆኑን አንሰተዋል፡፡ በዚህም የልህቀት ማዕከሉ በብቁ የሰው ሀይል እና በቴክኖሎጂ የተሟላ እንዲሆን ተደርጓል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል ጋዜጠኛውን ብቻ ሳይሆን መገናኛ ብዙኃንን ጭምር እንዲያልቅ እንፈልጋለን ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ በጥናትና ምርምር፣ ስልጠናና በማማከር ሀገር በቀል እሳቤዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡ በዓለም ላይ ጋዜጠኝነት ከጥቅል ወደ ልዩ ዘጋቢነት እየተቀየረ መሆኑን በማስታወስ፤ ጋዜጠኞችን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በምርጫ፣ ውሃ፣ ፋይናንስ፣ ሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ አቬሽን ጋዜጠኝነትና መሰል ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በማሰልጠንና በማብቃት የምስክር ወረቀት እንዲያገኙ ይደረጋል ብለዋል፡፡ ማዕከሉ የምርጫ ጋዜጠኝነት ስልጠና በቅርቡ እንዲሚጀምር በመጥቀስ፤ ከስድስት ዩኒቨርሲቲዎች በመጡ 32 ፕሮፌሰሮች 11 የሥልጠና ሰነዶች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል፡፡ ለሶስት ወራት በሚሰጠው የምርጫ ጋዜጠኝነት ሥልጠና የተዘጋጁ ሰነዶች የኢትዮጵያ የምርጫ ታሪክ፣ ሚዲያና ዲሞክራሲ፣ ሚዲያና ብሔራዊ ጥቅም፣ ምርጫና የዓለም አቀፍ ሚዲያዎች ልምድ፣ እንዲሁም ሚዲያ ማህበረሰብና ባህል የሚሉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
የዲጂታላይዜሽን አገልግሎትን ለማጠናከር በሚደረገው ሂደት የሳይበር ደህንነትን ማረጋገጥ ይገባል
Oct 18, 2025 124
ጅማ ፤ጥቅምት 8/2018 (ኢዜአ)፡-የዲጂታላይዜሽን አገልግሎትን ለማጠናከር በሚደረገው ሂደት የሳይበር ደህንነትን ማረጋገጥ እንደሚገባ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር አስታወቀ። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር "የሳይበር ደህንነት የዲጂታል ኢትዮጵያ መሰረት" በሚል መሪቃል በጅማ ከተማ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሂዷል። የሳይበር ደህንነት ወርን በማስመልከት በተዘጋጀው በዚህ የውይይት መድረክ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት የተሳተፉ ሲሆን መድረኩም ግንዛቤ የመፍጠር ዓላማ እንዳለው ተመላክቷል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ ዲጂታል የመንግስት አገልግሎትን ለማስፋፋት ትኩረት ከመስጠት ባለፈ በሳይበር ደህንነት ላይ ጠንካራ ሥራ እየተሰራ ነው። ተቋማቱም የሳይበር ደህንነት ተጋላጭነታቸውን በመቀነስ አስተማማኝ እና ዘመናዊ አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ ትኩረት መሰጠቱን ዳይሬክተሯ ተናግረዋል። የዲጂታላይዜሽን አገልግሎት ለህዝብ ተደራሽ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት የሳይበር ደህንነትን ማረጋገጥ የሁልግዜም ተግባር ሊሆን እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። የሳይበር ደህንነትን ወርም ይህን እውን ለማድረግና የሀሰተኛ የመረጃ ስርጭትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለመፍጠር በማለም እንደሚከበር አክለዋል። በተለይም የስማርት ከተማን በመገንባት ፈጣንና ዘመናዊ አገልግሎቶችን ለመስጠትና ብልሹ አሰራርን ለማስወገድ የዲጂታል አገልግሎት ጉልህ አስተዋጾ እንዳለው ነው የገለጹት። ለተግባራዊነቱም ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመተባበር የዲጂታላይዜሽን አገልግሎትን ለማጠናከርና የስማርት ከተሞችን ለማስፋፋት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በብልጽግና ፓርቲ የጅማ ከተማ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ዋሴ ግርማ በበኩላቸው እንዳሉት በጅማ ከተማ ዲጂታል አገልግሎቶችን በመተግበር ስማርት ከተማ ለመገንባት እየተሰራ ነው። ለእዚህም ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር በከተማዋ ፈጣንና ዘመናዊ አገልግሎት ለመስጠት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በመድረኩ የተለያዩ ተቋማት የሥራ ሀላፊዎች እንዲሁም የፌደራል፣ የክልልና የከተማ አስተዳደሩ ባለድርሻ አካላት መሳተፋቸው ታውቋል።
በአፍሪካ ሁለንተናዊ ልማትን ለማረጋገጥ የወጣቱን የፈጠራና የቴክኖሎጂ ክህሎት ማሳደግ ይገባል
Oct 17, 2025 157
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በአፍሪካ ዘላቂና ሁለንተናዊ ልማትን ለማረጋገጥ የወጣቱን የፈጠራና የቴክኖሎጂ ክህሎት ማሳደግ እንደሚገባ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) ገለጹ። ከጥቅምት 3 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው 2ኛው የአፍሪካ የክህሎት ሳምንት ዛሬ ተጠናቋል። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) መርሃ ግብሩ፣ በአፍሪካ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠናን ጥራት ለመጠበቅና ተደራሽነቱን ለማስፋት ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን ምርጥ ተሞክሮ ያካፈለችበት እና ከሌሎች ልምድ የወሰደችበት ስኬታማ መድረክ እንደነበርም ገልጸዋል። የአፍሪካ መጻዒ እድል የሚወሰነው በወጣቶች ላይ በምንሰራው ሁሉን አቀፍ የክህሎት ልማት ስራ ልክ ነው ሲሉም ገልጸዋል። በአፍሪካ ዘላቂና ሁለንተናዊ ልማትን ለማረጋገጥ የወጣቱን የፈጠራና የቴክኖሎጂ አቅም ማሳደግ እንደሚገባም አመላክተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለሰው ሀብት ልማት ስራ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች እንደምትገኝ ጠቁመው፤ በቀጣይም ከአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ጋር በማስተሳሰር አጠናክራ እንደምትቀጥል አስታውቀዋል። በመድረኩ ማጠቃለያም የአፍሪካ አገራት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሰው ሀብት ለማፍራት በጋራ የሚሰሩበት አቅጣጫ መቀመጡንም አመላክተዋል። በአፍሪካ ህብረት የትምህርት፣ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ፈጠራ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጋስፓርድ ዳንያንክምቦና በበኩላቸው፤ የቴክኒክና ሙያ ትምህርት የእድገት ማሳለጫ ዘርፍ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም የአፍሪካ አገራት በአፍሪካ ህብረት 2063 አጀንዳ መሰረት ቅንጅት በመፍጠር ዘርፉን በማሳደግ አለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሰው ሃይል ማፍራት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡ የዛሬ የአፍሪካ ወጣቶች ነገን ፈጠራ በታከለበት ሁኔታ መምራትና ለውጥ የማምጣት ሃላፊነት እንደተጣለባቸው አንስተው፤በዚህ ሒደት ውስጥ ከጎናቸው እንደሚሆኑ አረጋግጠዋል፡፡ ከኢኳቶሪያል ጊኒ የመጡ የመድረኩ ተሳታፊ ዮላንዳ አሱሙ በበኩላቸው፤ ሁለተኛው የአፍሪካ የክህሎት ሳምንት በርካታ ልምዶችን የተለዋወጥንበት ነበር ብለዋል፡፡ የአፍሪካ ሁለተኛው ክህሎት ሳምንት እጅግ አስተማሪና ትልቅ ግንዛቤ የወሰድንበት ሆኖ አልፏል ያለው ደግሞ ከሴኔጋል የመጣው ወጣት ደቪድ ሞዓድ ነው፡፡
ለዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ የሚያስፈልገውን የሰለጠነ የሰው ኃይል የማፍራት ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል
Oct 17, 2025 91
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 7/2018 (ኢዜአ)፡-በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ ለሚፈጠሩ የስራ እድሎች የሚያስፈልገውን የሰለጠነ የሰው ኃይል የማፍራት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የስራና ክህሎት ሚኒስቴር አስታወቀ። የስራና ክህሎት ሚኒስቴር"የነገው የስራ ዓለም"በሚል መሪ ሃሳብ ቀጣሪ ድርጅቶችን እና ተመራቂ ተማሪዎችን ለማገናኘት ያዘጋጀው አውደ ርዕይ እየተካሄደ ነው። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታው ሰለሞን ሶካ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፥ የነገው የስራ ዓለም ከቴክኖሎጂ እድገት ጋር የተጣጣመ እንዲሆን ከወዲሁ ዝግጅት እየተደረገ ነው። ዘርፉ የሚፈልገውን የሰው ኃይል ለማዘጋጀት ገበያ መር የክህሎት ልማት እና ክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራ ላይ በስፋት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ዜጎች ወደፊት በሚኖሩ የስራ እድሎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ መንግስት የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በኢትዮጵያ የተማሩ ወጣቶች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ተከትሎ ሰፋፊ የስራ እድሎችን ለመፍጠር ሁለንተናዊ ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑን ገልፀዋል። የመንግስትና የግሉን ዘርፍ ትብብርና አጋርነትን መሰረት ያደረጉ የስራ ስምሪቶችን በማስፋት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል። አውደ ርዕይውን በትብብር ያዘጋጀው አፍሪ ወርክ ድርጅት ዋና ስራ አስኪያጅ ስመኝ ታደሰ በበኩላቸው፥ አውደ ርዕዩ በቀጣይ ኢትዮጵያ ውስጥ ለሚኖሩ የስራ እድሎች ቀድሞ ዝግጅት በሚደረግባቸው መስክ ላይ ለመወያየት ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም ወጣቱ የሰው ሰራሽ አስተውሎትን መሰረት ካደረጉ ቴክኖሎጂዎች ጋር እንዲተዋወቅ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ለመወያየት የተዘጋጀ መሆኑን ነው የገለጹት። ቀጣሪ ድርጅቶችን ወክለው የተገኙት እሌኒ አምሀ እና ቤቴል ተስፋዬ በበኩላቸው አውደ ርዕዩ ከተለያዩ ድርጅቶች፣የስራ እድል ከሚፈልጉ ዜጎችንና ባለድርሻ አካላት ጋር በቀጥታ ለመገናኘት ዕድል የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል። ከስራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ ስራ በመፍጠር ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል ስራ መጀመራቸውን ጠቅሰዋል።
በኢትዮጵያ 100 ከተሞችን ተደራሽ የሚያደርግ የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ተግባራዊ ሊደረግ ነው
Oct 17, 2025 113
ጎንደር ፤ ጥቅምት 7/2018 (ኢዜአ)፡-በኢትዮጵያ 100 ከተሞችን ተደራሽ የሚያደርግ የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ መሆኑን የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት አስታወቀ፡፡ ኢንስቲትዩቱ ጎንደር ከተማን የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል ፕሮጀክት የመግባቢያ ሰነድ ስምምነት ዛሬ ተፈራርሟል፡፡ የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ በላቸው ፀሐይ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያን ታላላቅ ከተሞች ዘመኑን የዋጀ የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው፡፡ ኢንስቲትዩቱ በ10 ዓመት ውስጥ 100 ከተሞችን ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ስትራቴጂ ነድፎ ወደ ስራ መግባቱን ጠቁመው በአሁኑ ወቅት አዲስ አበባን ጨምሮ በርካታ የክልል ከተሞችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል፡ በአማራ ክልል የደብረ ብርሃንና የኮምቦልቻ ከተሞች የቴክኖሎጂው ተጠቃሚ መሆናቸውን አንስተው፤ በደሴና ወልዲያም ፕሮጀክቱን ተግባራዊ ለማድረግ መታቀዱን ተናግረዋል፡፡ የከተሞች የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ከተሞች ወደ ስማርት ሲቲ የሚያደርጉትን የቴክኖሎጂ ሽግግር የሚያፋጥን ከመሆኑም በላይ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም መዳረሻ ለሆኑ ከተሞች የላቀ አበርክቶ አለው፡፡ ዲጂታል የአድራሻ ስርዓት መኖሪያ ቤቶችን፣ መንገዶችንና የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ያሉበትን መገኛ ቦታ ርቀትና አቅጣጫ በቀላሉ ለማመልከት የሚያስችል ዘመናዊ ቴክኖሎጂ እንደሆነም አብራርተዋል፡፡ ዲጂታል የአድራሻ ስርዓት ለከተሞች ፈጣን እድገትና ለውጥ ቁልፍ የቴክኖሎጂ መሳሪያ ነው ያሉት የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ናቸው፡፡ የጎንደር ከተማ ሰባት ታላላቅና ታዋቂ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎች እንዳሏት ጠቅሰው፤ እነዚህን የቱሪዝም የመስህብ ሀብቶች በማስተዋወቅ ቱሪስቶች ስፍራዎቹን በቀላሉ እንዲጎበኙ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ቴክኖሎጂ ነው ብለዋል፡፡ ከተማ አስተዳደሩ ለፕሮጀክቱ ተፈጻሚነት ከኢንስቲትዩቱ ጋር በቅርበት የሚሰራ ሲሆን በመጪው ጥር ወር በከተማው በድምቀት ለሚከበረው የጥምቀት በዓል ቴክኖሎጂውን ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በመግባቢያ ስምምነት ሰነዱ ላይ የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ የኢንስቲትዩቱ የስራ ኃላፊዎችና ተመራማሪዎች ተገኝተዋል፡፡
በተያዘው በጀት ዓመት ከ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ስማርት ቴክኖሎጂዎችን ለደንበኞች ለማቅረብ ዝግጅት ተደርጓል - ኢትዮ ቴሌኮም
Oct 17, 2025 125
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 7/2018(ኢዜአ)፦ በተያዘው በጀት ዓመት ከ 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ስማርት የአገልግሎት ማሳለጫ ቴክኖሎጂዎችን ለደንበኞች ለማቅረብ ዝግጅት መደረጉን የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ። የኢትዮ ቴሌኮም በኢትዮጵያ የኢንተርኔት ተደራሽነትን ይበልጥ ለማሳደግ የሚረዳ ዘኔክሰስ የተሰኘ አገልግሎት በይፋ አስጀምሯል። የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ፥ የኢትዮጵያን ዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ እውን ለማድረግ ኢትዮ ቴሌኮም ለቴሌኮምና ዲጂታል መሰረተ ልማት ግንባታ ትኩረት መስጠቱን ተናግረዋል። ባለፉት ስድስት ዓመታትም የአራተኛውና አምስተኛው ትውልድ ኔትወርክ አገልግሎት፣ ክላውድ፣ የቴሌብርና ዘመን ገበያን ጨምሮ ሥራ ላይ የዋሉ መሰረተ ልማቶች ትልቅ አቅም እየፈጠሩ መሆኑን ጠቅሰዋል። የደንበኞችን ቁጥር ወደ 100 ሚሊዮን ለማድረስ ግብ መጣሉን ገልጸውም ከዚሁ ውስጥ 69 ሚሊዮን ደንበኞች የሞባይልና ብሮድባንድ ኢንተርኔት ተጠቃሚ ለማድረግ ስትራቴጂ ተነድፎ ወደ ሥራ መገባቱን አብራርተዋል። በኢትዮጵያ 85 ነጥብ 9 ሚሊዮን የኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞች እንዳሉ አመልክተው፤ ከእነዚህ ውስጥ 47 ሚሊዮኑ ብቻ ኢንተርኔትን እንደሚጠቀሙ አስታውቀዋል፡፡ ለዚህም የተለያዩ ምክንያቶች ቢኖሩም የመጠቀሚያ ስማርት መሳሪያዎች ዋጋ መወደድ ዋነኛው ምክንያት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም ይህንኑ ታሳቢ በማድረግ ዘ ኔክሰስ የተሰኘ አገልግሎት ይፋ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ የክላውድ ቴክኖሎጂን የሚጠቀሙ የእጅ ስልኮች፣ ላፕቶፖች፣ ታብሌቶችና ወርክ ስቴሽኖች በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ ማቅረቡን ተናግረዋል። መሳሪያዎቹን የሚጠቀሙ ደንበኞች የኢትዮ ቴሌኮምን ክላውድ በቀጥታ በመጠቀም አገልግሎት ማግኘት የሚያስችላቸው መሆኑንም አብራርተዋል፡፡ በተያዘው በጀት ዓመት ከ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ስማርት ቴክኖሎጂዎችን ለማቅረብ ዝግጅት መደረጉን ጠቁመው ይህም የኢንተርኔት ተደራሽነትን በከፍተኛ ሁኔታ ያሻሽላል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅት ግብርና፣ ዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎት፣ ትምህርትን ጨምሮ የተለያዩ መንግሥታዊ አገልግሎቶች በኢንተርኔት እንደሚሰጡ ጠቁመው፤ በዚህ ረገድ ዘ ኔክሰስ አገልግሎት ወደ ስራ መግባት ትልቅ ፋይዳ አለው ብለዋል፡፡ ዘኔክሰስ አገልግሎት ተቋማትን ተወዳዳሪ ለማድረግ እንዲሁም ቀልጣፋ ዘመናዊ አገልግሎቶችን ተደራሽ እንዲያደርጉ ትልቅ ሚና እንደሚጫወትም አስረድተዋል።
ስማርት ድሬዳዋን ዕውን ለማድረግ እና መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በስፋት ለማዳረስ ጥረት እየተደረገ ነው
Oct 16, 2025 125
ድሬዳዋ፤ ጥቅምት 6/2018(ኢዜአ)፡- ስማርት ድሬዳዋን ዕውን ለማድረግ እና መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በጥራትና በስፋት ለማዳረስ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ገለጹ። በድሬዳዋ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ለሚገነባው የአይ ሲ ቲ ትምህርትና ስልጠና ልህቀት ማዕከል ዛሬ የመሠረት ድንጋይ ተቀምጧል። የመሠረት ድንጋዩን ያስቀመጡት ከንቲባ ከድር ጁሃር፣ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአስተዳደሩ ምክርቤት የመንግስት ተጠሪ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ እና የካቢኔ አባላት ናቸው። በዚህ ወቅት ከንቲባው እንደገለጹት፤ ማዕከሉ ስማርት ድሬዳዋን ዕውን ለማድረግ ለሚከናወነው ሥራ ወሳኝ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። የልህቀት ማዕከሉ በተጨማሪም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በጥራትና በስፋት ለማዳረስ በሚደረገው ጥረት መሠረታዊ ሚና እንደሚኖረው ነው ያመለከቱት። ባለ አምስት ወለል የሚሆነው የልቀት ማዕከል ግንባታ ሥራ በተያዘለት የ14 ወራት ጊዜ ውስጥ በጥራትና በፍጥነት ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር ይደረጋል ብለዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአስተዳደሩ ምክር ቤት የመንግስት ተጠሪ ኢብራሂም ዩሱፍ በበኩላቸው ለድሬዳዋ ዲጂታል የለውጥ ጉዞ ዕውን መሆንና በዘርፉ ሥራ ፈጣሪ ትውልድ ለመገንባት ማዕከሉ የጎላ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተናግረዋል። የድሬዳዋ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዲን አቶ ሰላሃዲን አብዱልሃሚድ በበኩላቸው፤ ማዕከሉ በውስጡ 42 ክፍሎች እንደሚኖሩት ገልጸዋል። የኮምፒውተር ላቦራቶሪ፣ የምርምርና የመማሪያ ክፍሎች፣ እንዲሁም የዲዛይን ስቱዲዮ፣ የኮንፍረንስ እና የዲጂታል ቤተ-መጻህፍትን እንደሚያካትም ተመላክቷል።
ኢትዮ ቴሌኮም የኢንተርኔት አገልግሎትን ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ የሚረዳ ዘ ኔክሰስ የተሰኘ አገልግሎት ይፋ አደረገ
Oct 16, 2025 136
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 6/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮ ቴሌኮም የኢንተርኔት አገልግሎትን ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ የሚረዳ ዘ ኔክሰስ የተሰኘ አገልግሎት ይፋ አድርጓል። የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ አገልግሎቱን አስመልክተው ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ በዚሁ ወቅት፤ በኢትዮጵያ 85 ነጥብ 9 ሚሊዮን የኢትዮ ቴሌኮም ደንበኞች እንዳሉ አመልክተው፤ ከእነዚህ ውስጥ 47 ሚሊዮኑ ብቻ ኢንተርኔት እንደሚጠቀም አስታውቀዋል፡፡ ለዚህም የተለያዩ ምክንያቶች ቢኖሩም የመጠቀሚያ ዲቫይሶች (መሳሪያዎች) ዋጋ መወደድ ዋነኛው ምክንያት መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም ይህንኑ ታሳቢ በማድረግ ዘ ኔክሰስ የተሰኘ አገልግሎት ይፋ ማድረጉን ጠቁመዋል፡፡ አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ የክላውድ ቴክኖሎጂን የሚጠቀሙ ፊውቸር ፎኖች(የእጅ ስልኮች) ላፕቶፖች፣ ታብሌቶችና ዴስክ ቶፕ ኮምፒዩተሮች በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ ማቅረቡን ገልጸዋል። መሳሪያዎቹን የሚጠቀሙ ደንበኞች የኢትዮ ቴሌኮምን ክላውድ በቀጥታ በመጠቀም የኢንተርኔት አገልግሎት ማግኘት የሚያስችላቸው መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ግብርና፣ ዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎት፣ ትምህርትን ጨምሮ የተለያዩ መንግሥታዊ አገልግሎቶች በኢንተርኔት እንደሚሰጡ ጠቁመው፤ በዚህ ረገድ ዘ ኔክስ አገልግሎት ወደ ስራ መግባት ትልቅ ፋይዳ አለው ብለዋል፡፡
ማዕከሉ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ብቁ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማትና ባለሙያዎችን ማፍራት ያስችላል
Oct 16, 2025 128
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 6/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ብቁ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማትና ባለሙያዎችን ለማፍራት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሳምሶን መኮንን(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል ማስጀመሪያ መርኃ ግብር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ተካሂዷል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሳምሶን መኮንን(ዶ/ር) የመገናኛ ብዙኃን ለሀገር ሁለንተናዊ ዕድገትና ብሔራዊ ጥቅም መከበር የማይተካ ሚና እንዳላቸው ገልጸዋል። የልህቀት ማዕከሉ ብሔራዊ ጥቅምን ማዕከል ያደረገ ጋዜጠኝነትን የተካነ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያ ለማፍራት ያግዛል ብለዋል፡፡ በብቁ የሰው ኃይልና ቴክኖሎጂ የተደራጀ መሆኑን ገልጸው፤ ከፖሊሲ አውጪዎችና ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር በትብብር እንደሚሰራም ነው ያስታወቁት፡፡ የምርጫ ጋዜጠኝነት ሥልጠና በቅርቡ እንደሚጀምር በማንሳት፤ ማዕከሉ በውሃ፣ በማዕድን፣ በአየር ንብረት፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ በአቪየሽንና በሌሎችም ዘርፎች ስልጠና እንደሚሰጥ ገልጸዋል፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሳሙኤል ክፍሌ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ጋዜጠኝነት ከሙያ ዕድገት ጋር የተጣጣመ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ፣ ብልጽግናን ዕውን ለማድረግ፣ የወል ትርክትን ለመገንባትና ህብረ ብሔራዊ አንድነትን ለማረጋገጥ ግልጽ ሀሳብ፣ ብቁ ተቋማትና ብቁ ባለሙያ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ የጋዜጠኝነት ሙያን በማሳደግ ብሔራዊ ጥቅምን የማስከበሪያ መሳሪያ ለማድረግ በዩኒቨርሲቲዎች የሚሰጠው መደበኛ ትምህርት ብቻ በቂ እንዳልሆነ ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነት ሙያን ለማዳበርና የመገናኛ ብዙኃንን አቅም ለማጎልበት ወቅቱን የዋጁ ስልጠናዎችና የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት የሚሰጥበት አሰራር ዘርግቷል ብለዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን ትምህርት ክፍል መምህር እና አማካሪ አንተነህ ጸጋዬ(ዶ/ር) እንዳሉት ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት በነጻነት እንዲሰሩ የሚያስችሉ በርካታ የፖሊሲና የህግ ማሻሻያዎች መደረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ ይሁን እንጂ መገናኛ ብዙኃኑ አፋኝ ህጎች ተሻሽለው ምቹ የሥራ ምህዳር ቢፈጠርም ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም የሚጠበቅባቸውን ያህል አልተወጡም ብለዋል፡፡ በመሆኑም ችግሩን ለመፍታት የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል በሙያዊ አቅም ግንባታ አንደኛው የመፍትሔ አማራጭ ሆኖ እንደሚያገለግል ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል ብሔራዊ ጥቅምን ያማከለ የሚዲያ ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የማይተካ ሚና አለው - አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ
Oct 16, 2025 108
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 6/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል ብሔራዊ ጥቅምን ያማከለ የሚዲያ ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የማይተካ ሚና እንዳለው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ የሚዲያ ልህቀት ማዕከል ማስጀመሪያ መርኃ ግብር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ተከናውኗል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ መገናኛ ብዙሃን ትኩስና ወቅታዊ መረጃዎችን በማቅረብ ለሰላም ግንባታና ለህብረተሰብ አመለካከት ለውጥ የማይተካ ሚና አላቸው። መንግሥት ህጎችንና አሠራሮችን በማሻሻል የመገናኛ ብዙሃንን በአይነትና በቁጥር ማስፋት መቻሉን ገልጸዋል። በዚህም መገናኛ ብዙሃኑ ታላላቅ ሀገራዊ ጉዳዮች በተለይም በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ህዝቡን በንቃት በማሳተፍ፤ ሀገራዊ ምርጫው ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ በማድረግ ገንቢ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያን ዕድገትና ብልፅግና ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን ሚና እየተወጡ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም በሰላም፣ በልማት፣ በሕብረ ብሔራዊ አንድነትና ሀገር ግንባታ ላይ ገንቢ ሚናቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል፡፡ የዓለም አቀፍና ሀገር አቀፍ የሚዲያ አውድ ተቀይሯል ያሉት አፈጉባኤው፤ የዲጂታል ጋዜጠኝነት መስፋፋት የጋዜጠኝነት ሥነ ምግባርን የጣሱ አካላት ግን ተገቢ ያልሆነ ይዘት እንዲያሰራጩ በር መክፈቱን ገልጸዋል፡፡ ይህ ዓይነቱ አካሄድ ደግሞ ሃሰተኛ መረጃና የጥላቻ ንግግርን በማሰራጨት በህዝብ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳል ብለዋል፡፡ በመሆኑም መገናኛ ብዙሃን ሙያዊ ሥነ ምግባርን በጠበቀ መልኩ የሀገርና የህዝብ ጥቅምን የማስከበር ተልዕኳቸውን እንዲወጡ አፅንኦት ሰጥተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል የጋዜጠኝነት ሙያ ስነ-ምግባር የተላበሰና ኢትዮጵያን ማዕከል ያደረገ የሚዲያ ስርዓት ለመፍጠር፣ ብሔራዊ ጥቅምን ማዕከል ያደረገ የሚዲያ ተደራሽነትን ለማስፋት ያግዛል ብለዋል። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም ለማዕከሉ እድገትና ለመገናኛ ብዙሃን ምህዳር መስፋት አስፈላጊውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል፡፡
መገናኛ ብዙኃን ሕብረ ብሔራዊ አንድነትንና ሀገራዊ ብልጽግናን የማስረጽ ተልዕኳቸውን መወጣት አለባቸው
Oct 16, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 6/2018(ኢዜአ)፦ መገናኛ ብዙኃን ሕብረ ብሔራዊ አንድነትንና ሀገራዊ ብልጽግናን የማስረጽ ተልዕኳቸውን መወጣት እንዳለባቸው የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙዓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት አስገነዘቡ፡፡ የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል ማስጀመሪያ መርኃ ግብር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቅጥር ግቢ ተካሂዷል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙዓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ በሀገራችን ያለው ጋዜጠኝነት ኢትዮጵያን መምሰል አለበት። በኢትዮጵያ ያሉ የግልም ይሁኑ የህዝብ ወይም የሃይማኖት መገናኛ ብዙሃን በአራት ጉዳዮች ላይ ልዩነት ሊኖራቸው አይገባም ብለዋል። የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቅ በማንኛውም መገናኛ ብዙሃን የሚሰራ ጋዜጠኛ ሊረሳው የማይገባ ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል። መገናኛ ብዙሃን የኢትዮጵያን ሕብረ ብሔራዊ አንድነት የሚያጠናክሩ፣ የህዝብን ትብብርና አንድነት የሚያሳዩ መሆን አለባቸው ብለዋል። የወል ትርክትን መገንባት እና ኢትዮጵያ መበልጸግ አለባት የሚለውን ሀገራዊ የብልጽግና ዕሳቤ ታሳቢ አድርገው መስራት እንዳለባቸውም አፅንኦት ሰጥተዋል። የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን መገናኛ ብዙኃንን ለመደገፍና ለማብቃት ያደረገው ተግባር የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው፤ በኢትዮጵያ ፈቃድ የወሰዱ መገናኛ ብዙኃን ኢትዮጵያን መምሰል አለባቸው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያን ማበልጸግ ዘመናትን የተሻገረ የልሂቃን ዕሳቤ መሆኑን ያነሱት አማካሪ ሚኒስትሩ፤ ጋዜጠኝነት የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም የሚያስጠበቅ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ መገናኛ ብዙኃን በሁሉም ህብረተሰብ ዘንድ ሕብረ ብሔራዊ አንድነትና ብልጽግናን የማስረጽ ተልዕኳቸውን መወጣት እንዳለባቸው ነው ያስገነዘቡት፡፡ ብሔራዊ ጥቅምን፣ ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን፣ የወል ትርክትና ሀገራዊ ብልፅግናን በማስረጽ ተልዕኳቸው ላይ ልዩነት ሊኖራቸው አይገባም ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሚዲያ ልህቀት ማዕከል የመገናኛ ብዙኃን ዘርፉ የሚጠይቀውን ስልት፣ ፈጠራና ብቃት ለማሟላት ተጨማሪ አቅም እንደሚሆንም ገልጸዋል፡፡ ጋዜጠኝነት ተምሮ የሚገባበት ብቻ ሳይሆን በየጊዜው ብቃቱ የሚለካበት፣ የሙያ ፈቃድ የሚሰጥበትና የሚታደስበት መሆን አለበት ብለዋል፡፡ በመርኃ ግብሩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ፣ የፌደራል መንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች፣ የተለያዩ መገናኛ ብዙሃንና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሃላፊዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
የተቋማትን አገልግሎት አሰጣጥ ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ፈጣንና ቀልጣፍ ለማድረግ የሚያስችል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው- ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Oct 16, 2025 106
ባሕርዳር ፤ ጥቅምት 6/2018(ኢዜአ) ፡- በአማራ ክልል የተቋማትን አገልግሎት አሰጣጥ ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ፈጣንና ቀልጣፍ ለማድረግ የሚያስችል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። ''የሳይበር ደህንነት የዲጂታል ኢትዮጵያ መሰረት'' በሚል መሪ ሃሳብ 6ኛው ሀገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር በባሕር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፤ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ዘመኑን በሚመጥን መንገድ በቴክኖሎጂ የታገዘና ደህንነቱ የተጠበቀ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም በክልሉ የተቋማትን አገልግሎት አሰጣጥ ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ፈጣንና ቀልጣፍ ለማድረግ የሚያስችል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ ቴክኖሎጂን በማልማትና በመተግበር የተጀመሩ ስራዎች በትብብርና በቅንጀት የሚተገበሩ መሆኑን ጠቅሰው ለዚህም የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና እገዛ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። የኢንፎርሜሸን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በከፍተኛ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ትግበራ ላይ መሆኗን ጠቅሰው ፤ በዚሁ ልክ የሳይበር ደህንነት ጥበቃ ስራ ልዩ ትኩረት የተሰጠው መሆኑን አስረድተዋል። የመልካም አስተዳደር ችግሮችን የመፍታት፣ ሙስና እና ብልሹ አሰራርን በማስቀረት ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ተደራሽ ማድረግ ጊዜው የሚጠይቀው ጉዳይ መሆኑን አንስተው፤ ከዚሁ ጋር በተገናኘ የሳይበር ደህንነትን ማስጠበቅ የግድ መሆኑን ገልጸዋል። የሳይበር ደህንነት ወር የመከበሩ ዓላማም ተቋማትና አጠቃላይ ሕብረተሰቡ በሳይበር ደህንነት ላይ የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖረው ለማስቻል መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የሀሰተኛ መረጃ ስርጭትን መከላከልና መቆጣጠር ብሎም በዲጂታላይዜሽን የስማርት ከተሞች እድገት ጉዞ ላይ የተቋማትን የሳይበር ጥቃት ተጋላጭነት በመቀነስ ዲጂታል ኢትዮጵያን ትልም ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል። 6ኛው ሀገር አቀፍ የሳይበር ደህንነት ወር ከጥቅምት 1 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም በተለያዩ መርሀ ግብሮች መከበሩ የሚቀጥል መሆኑ ታውቋል።
በአፋር ክልል የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የሚያግዝ የዲጂታል አገልግሎት ተዘርግቷል
Oct 15, 2025 159
ሰመራ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የሚያግዝ የዲጂታል አገልግሎት መዘርጋቱን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ የጭፍራ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የዲጂታላይዝ አገልግሎት ዛሬ ወደ ስራ ገብቷል። በአገልግሎቱ ማስጀመሪያ ስነ ስርአት ላይ የተገኙት የአፋር ክልል ጤና ቢሮ ኀላፊ አቶ ያሲን ሃቢብ እንደተናገሩት በክልሉ የጤና አገልግሎትን ጥራትና ተደራሽነት በማረጋገጥ የተገልጋዩን እርካታ ለማሳደግ እየተሰራ ነው። የጤና አገልግሎቱን ጥራትና ተደራሽነት ለማረጋገጥ የዲጂታል መረጃ አያያዝንና የሰው ሀይል አቅም ግንባታ ላይ መሰራቱን አክለዋል። ይህም የጤናውን ዘርፍ በተጠናከረ መረጃ በመደገፍ ለህብረተሰቡ የሚሰጠውን አገልግሎት አስተማማኝና ፈጣን ለማድረግ እንደሚያስችል ተናግረዋል። ዛሬ በይፋ ስራ የጀመረው የጭፍራ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የዲጂታላይዜሽን አገልግሎትም የዚሁ ጥረት አካል ነው ብለዋል። ከወረቀት ንክኪ ነጻ የሆነው ይህ አገልግሎት የተደራጀ የጤና መረጃን በቀላሉ ለህክምና ተግባሩ ለማዋል እንደሚያግዝ ተናግረዋል። አገልግሎቱን በቀጣይም ወደ ሌሎች ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች የማስቀጠል ተግባር እንደሚከናወን አመላክተዋል። የጭፍራ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አሊ አርባ በበኩላቸው በቴክኖሎጂ የተደገፈው የሆስፒታሉ አገልግሎት መረጃን በአግባቡ በማደራጀት ግልጽነትን ከመፍጠር ባለፈ ወረፋን የሚያስቀር መሆኑን ተናግረዋል። የጭፍራ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ መሐመድ አሚን ኡመር እንዳሉት በይፋ የተጀመረው አገልግሎት ለህክምና አሰጣጥ መቀላጠፍ፣ ለጥናትና ምርምር የተደራጁ መረጃዎችን ለማግኘት እንደ መረጃ ቋት ሆኖ ያገለግላል። በተለይም የህክምና አገልግሎትን ለማቀላጠፍ መረጃን በቀላሉ ለህክምናው ባለሞያ ተደራሽ በማድረግ ታካሚው ተገቢውን አገልግሎት እንዲያገኝ የሚያስችል ነው ብለዋል። በጤናው ዘርፍ በቴክኖሎጂ የተደገፈ ጥራት ያለውና አስተማማኝ አገልግሎት ለመስጠት ተጨማሪ እቅም እንደሚሆን ተናግረዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ወቅቱን የጠበቀና ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል የዲጂታል ስርዓት አስጀመረ
Oct 15, 2025 184
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፡- የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተቋማዊ አሰራሩን በማዘመን ወቅቱን የጠበቀና ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል የዲጂታል ስርዓትን ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ያበለጸገውን ዲጂታል የሰነድና ማህደር አስተዳደርና ወረቀት አልባ የአሰራር ስርዓትን (record management and smart paperless office) ዛሬ ይፋ አድርጓል። ሚኒስቴሩ በወረቀት አልባ ስማርት አሰራርና የዲጂታል የሰነድ ልውውጥና አያያዝ ስርዓት ላይ ያተኮረ ስልጠና መስጠት ጀምሯል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ሚኒስቴሩ አንጋፋነቱን የሚመጥን በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀልጣፋ የአሰራር ሥርዓት አልነበረውም፡፡ አሁን ላይ የተቋማዊ ሪፎርሙ አካል የሆነ የዲጂታል አሰራር ትግበራ መጀመሩን ገልጸው፥ ለዚህም ከኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ዲጂታል ስርዓት ማልማቱን ገልጸዋል፡፡ የሰነድና ማህደር አስተዳደር ስርዓቱ በሚኒስቴሩ ከመዝገብ አያያዝ እስከ ሚሲዮኖች የመረጃ ልውውጥ ድረስ የነበረውን የወረቀት አሰራር በማስቀረት ፈጣንና ቀልጣፋ የአገልግሎት ስርዓት መፍጠር ያስችላል ብለዋል፡፡ ስልጠናውም በዲጂታል የሰነድ አስተዳደር፣ በውስጥ እና በውጪ ግንኙነት እና በደብዳቤ ልውውጥ እንዲሁም በተቀላጠፈ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የጋራ አቅም ለመፍጠር ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። ወቅቱን የዋጀ ስርዓት ዘመናዊ የሰነድ አያያዝ ሥርዓት ከመፍጠር ባለፈ ጊዜንና ወጪን እንደሚቆጥብ ጠቁመዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ማስታወሻዎች፣ ጥናቶችና ታሪካዊ ፋይዳ ያላቸው ትልልቅ ሰነዶች የመነጩበት ተቋም መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ የሶፍትዌር ስርዓቱ የተቋሙን ተሞክሮዎችና ታሪኮች በዘመናዊ መንገድ ለመሰነድ የጎላ አበርክቶ እንዳለው አንስተዋል፡፡ የኢትዮጵያን የዲፕሎማሲና የውጭ ግንኙነት ልምድና አገልግሎት ለዲፕሎማቶች ለማሸጋገር የማይተካ ሚና እንዳለውም ገልጸዋል፡፡ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመረጃ ሀብትና የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ጀነራል ዳንኤል ዘገዬ በበኩላቸው፤ ዲጂታል ስርዓቱ የውስጥ አሰራርና የመረጃ ልውውጦችን ከወረቀት ነጻ በማድረግ በኤሌክትሮኒክ ስርዓት መሰነድ ያስችላል ብለዋል፡፡ ከብሄራዊ ቤተመጻህፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ ጋር በመተባበር ወደ ዲጂታል ስርዓት የሚገቡ ሰነዶችን የመለየትና ቦታ የማስያዝ ሥራዎች መከናወናቸውንም ገልጸዋል፡፡ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ተሰንደው መያዛቸው መረጃዎችን በቀላሉ ለውሳኔ አሰጣጥ፣ ለጥናትና ምርምር ግብዓት ጥቅም ላይ ለማዋል ያግዛል ብለዋል፡፡ የአሰራር ስርዓቱን ውጤታማ ለማድረግ ለተቋሙ የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች መሰጠት የጀመረው ስልጠና ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ በሳይበር ደህንነት ያገኘቻቸውን ውጤቶች በዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ መድረክ ላይ አቀረበች
Oct 15, 2025 199
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በሳይበር ደህንነት ያገኘቻቸውን ውጤቶች በዱባይ እየተካሄደ በሚገኘው ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ መድረክ ላይ አቅርባለች። 45ኛው የገልፍ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አውደ ርዕይ (ጂአይቴክስ) በዓለም የንግድ ከተማ በሆነችው ዱባይ እየተካሄደ ይገኛል። ይህ ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች፣ የመንግስት ተቋማት፣ ጀማሪ ስራ ፈጣሪዎች፣ ባለሀብቶች፣ ኢኖቬተሮች እና ተመራማሪዎችን በአንድ መድረክ ያገናኘ የ2025 ጂአይቴክስ መድረክ በተለይ በሰው ሰራሽ አስተውሎት እና የሳይበር ደህንነት ላይ ትኩረት ያደረጉ ውይይቶችም እየተደረጉበት ነው፡ ፡ ዛሬ በተካሄደው እና ትኩረቱን የመንግስትና የግል ተቋማት ትብብር ላይ ባደረገው ውይይት ኢትዮጵያም ተሞክሮዋን አካፍላለች። ከግሪክ፣ ኦማን እና የተባበሩት አረብ ኤምሬት የተሳተፉበት የዘርፉ ተወካዮች ጋር ተጋብዘው ንግግር ያደረጉት የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዳንኤል ጉታ ባለፉት ጊዜያት ኢትዮጵያ ዲጂታል ኢኮኖሚን ለመገንባት ያደረገቻቸውን ጥረቶች አስረድተዋል። አቶ ዳንኤል በማብራሪያቸው ባለፉት አምስት ዓመታት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በሚል የሀገሪቱን የዲጂታል ዘርፍ ለማሳደግ ሰፊ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች እንደተከናወኑ ገልጸዋል። አሁን ላይ በኢትዮጵያ ከ53 ሚሊዮን በላይ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች እንዳሉ ጠቁመው፤ የዘርፉ እድገት ዜጎች የዲጂታል አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም አንስተዋል። አቶ ዳንኤል በማብራሪያቸው የኢትዮጵያ ዲጂታል ዘርፍ በፍጥነት እያደገ ከመሆኑ ጋር በተገናኘ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመፍታት መንግስት አዳዲስ ፖሊሲዎችንና አሰራሮችን በፍጥነት ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝም አብራርተዋል። በተለይ በሳይበር ደህንነት ዘርፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በጋራ የሚሰሩበት ህብር የተሰኘ ቴክኖሎጂ በመፍጠር ወደ ስራ ለማስገባት እየተደረገ ያለውን ጥረት አስረድተዋል። ህብር በሳይበር ደህንነት ላይ የሚሰሩ ተቋማት፣ ግለሰቦች፣ የሳይበር ደህንነት አገልግሎት የሚፈልጉ ተቋማት እንዲሁም የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በጋራ እና በትብብር እንዲሰሩ የሚያስችላቸው ነው። በተጨማሪም የሳይበር ደህንነት ጥበቃ የሚል አዲስ ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጅቶ መንግስት፣ የግል ድርጅቶችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በትብብር እና በቅንጅት ሊሰሩ የሚችሉበትን ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑንም አቶ ዳንኤል ገልጸዋል። በቅርቡ የተሻሻለው የሳይበር ደህንነት ፖሊሲ አሁን እየመጡ ያሉ ስጋቶችን ለመከላከል ወሳኝ ሚና እንደሚጫወትም አመልክተዋል። የሀገሪቱ የዲጂታል 2030 ፖሊሲ ለሳይበር ደህንነት ልዩ ትኩረት የሰጠ መሆኑንም አቶ ዳንኤል በፖናል ውይይቱ ላይ ተናግረዋል። ከመድረኩ በኋላ ከPulse Of Africa ሚዲያ ጋር ቆይታ ያደረጉት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዳንኤል ጉታ ኢትዮጵያ በጂአይቴክስ ላይ መሳተፏ ሀገሪቷ በተለይ በቴክኖሎጂ፣ በሳይበር ደህንነት፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ ስማርት ሲቲ እና ሌሎች ዘርፎች ላይ እየሰራች ያለውን ውጤታማ ስራ ለማሳደግ ትልቅ እድል የሚፈጥር ነው ብለዋል። በ2025 ጂአይቴክስ ዱባይ ከ180 ሀገራት የተወጣጡ ከ6 ሺህ 500 በላይ አቅራቢዎች፣ ከ1 ሺህ 800 በላይ ጀማሪ ስራ ፈጣሪዎች እና ከ1 ሺህ 200 በላይ ባለሀብቶች እየተሳተፉ ይገኛሉ። ከጥቅምት 3 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እየተካሄደ በሚገኘው አውደ ርዕይ በተለይ ከሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) ጋር የተገናኙ ፈጠራዎች እና አገልግሎቶች በስፋት እየተዋወቁ ይገኛል። በተጨማሪም የጤና እና ባዮ ቴክኖሎጂዎች፣ ኮሙኒኬሽን፣ ሮቦቲክስ፣ የቀጣዩ ትውልድ ቴክኖሎጂዎች እና ሌሎች በርካታ ፈጠራዎች ለእይታ መቅረባቸውን የPulse Of Africa ሚዲያ መረጃ ያመለክታል።
ስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንዱስትሪ ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ የድሮን ቴክኖሎጂ ምርቶችን ማምረቱን አጠናክሮ ይቀጥላል
Oct 14, 2025 250
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 4/2018(ኢዜአ)፦ስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንደስትሪ ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ የድሮን ቴክኖሎጂ ምርቶችን ማምረቱን አጠናክሮ መቀጠሉን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አስታወቀ። ስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንዱስትሪ በሀገር ውስጥ ማምረት የጀመራቸውን ድሮኖች ምርት በማስፋት የድሮን ቴክኖሎጂን በምርምር እና ሥርፀት ለማሳደግ እንዲሁም ተግባራዊ ተሞክሮን ለማዳበር የሚያግዘውን ትብብር ለመፍጠር ከኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ከኢፌዴሪ አየር ኃይል፣ ከመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንደስትሪ ግሩፕ፣ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እና ከኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ጋር የመግባቢያ ሰነድ መፈራረሙን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ሲሳይ ቶላ ገልጸዋል፡፡ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ሲሳይ ቶላ በመርሐ-ግብሩ ላይ እንደገለጹት፥ ብሔራዊ ጥቅምን ከማስከበር እንዲሁም ካለው የላቀ ኢኮኖሚያዊና ስትራቴጂያዊ ፋይዳ አንጻር የድሮን ቴክኖሎጂን በራስ አቅም ማልማት ወቅቱ የሚጠይቀው ጉዳይ ነው፡፡ ይህን ከግምት ውስጥ በማስገባትም የካቲት 29 ቀን 2017 ዓ.ም በኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)ተመርቆ ስራ የጀመረው ስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንዱስትሪ ለደኅንነት፣ ለመረጃ ስምሪት፣ለሲቪልና ለወታደራዊ አገልግሎቶች የሚውሉ ድሮኖች ምርትን አጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል። የድሮን ቴክኖሎጂ በፈጣን ዕድገት ላይ የሚገኝ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ሲሳይ፤ እንደ ሀገር ብሔራዊ ጥቅምን ከማስጠበቅ፣ ኢኮኖሚያዊ እድገትን ከማሳለጥ እንዲሁም ወደፊት የሚቃጡ ጥቃቶችን ውጤት ከመወሰን አንፃር ያለውን ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ በመመዘን በድሮን ቴክኖሎጂ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን አገልግሎቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ ገልጿል፡፡ በዘርፉ ተወዳዳሪ ለመሆንና በሀገር ውስጥ የተፈጠረውን የድሮን ቴክኖሎጂ ዐቅም ለማጎልበት የአንድ ተቋም እንቅስቃሴ ብቻ በቂ ባለመሆኑ ከአምስቱ ተቋማት ጋር በትብበር እና አጋርነት ለመስራት ስምምነቱ ማስፈለጉን የአገልግሎት መስሪያ ቤቱ ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ሲሳይ አብራርተዋል፡፡ ስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንደስትሪ የሚያመርታቸውን ድሮኖች በዓይነትና በጥራት ለማሳደግ የድሮን ቴክኖሎጂ የሚጠቀማቸውን ስማርት ሴንሰሮች በተመለከተ ከአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ አስተዳደር፤ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የዘርፉን ምርምር ውጤቶችና የሰለጠነ የሰው ኃይል፤ በመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንደስትሪ በኩል ለውጊያ የሚውሉ ድሮኖች የሚታጠቋቸው ጦር መሳሪያዎች ምርትን፤ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ የካበተ የአቪዬሽን ዘርፍ ተሞክሮ እንዲሁም ከኢፌዴሪ አየር ኃይል በኩል ተግባራዊ ልምምድ ለመቅሰም ታልሞ የትብበር ስምምነቱ መፈረሙ ተመልክቷል፡፡ ከመግባቢያ ሰነድ ፊርማው በኋላ የስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንደስትሪና የድሮን ምርቶቹ የተጎበኙ ሲሆን፤ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሳሙኤል ክፍሌ ስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንዱስትሪ በዘርፉ የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማረጋገጥ እና በሀገር ውስጥ ያሉትን የተለያዩ ተቋማት እና ዩኒቨርሲቲዎች ዕውቀት፣ ልምድና ሀብት በመደመር ውጤታማነትን ለማረጋገጥ በትብብር ለመስራት የወሰደው ቁርጠኝነት የሚደነቅ ነው ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በዘርፉ በሚያደርጋቸው ምርምር እና ልማት እንዲሁም የሰው ኃይልን በማሰልጠን ከስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንደስትሪ ጋር በትብብር ለመስራት ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአቪዬሽን ዘርፍ ያለውን ተሞክሮ ማካፈል ብቻ ሳይሆን ወደፊት በስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንደስትሪ የሚመረቱ ድሮኖችን መጠቀም የሚችልበት ዕድሎች መኖራቸውንም ጠቁመዋል፡፡ በዓለማችን ሀገራት ውጥረት ውስጥ በገቡ ጊዜ ሉዓላዊነታቸውን ለማስከበር በሚያካሄዷቸው ማናቸውም ኦፕሬሽኖች ላይ የድሮን ቴክኖሎጂ ሚናው እያደገ መምጣቱን የጠቀሱት የመከላከያ ኢንጂነሪግ ኢንደስትሪ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ጌታቸው ሃይለማርያም፤ የሀገራችንን ሉዓላዊነት ለማስከበር ዘርፉን በራስ አቅም በተገቢው መንገድ ለመጠቀም በትብብር ለመስራት አጋጣሚው ተፈጥሯል ብለዋል፡፡ አነስተኛ እና መካከለኛ ድሮኖችን በማምረት ስራውን የጀመረ ስካይዊን ኤሮኖቲክስ ኢንደስትሪ እ.አ.አ በ2030 ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ያላቸው ትላልቅ ድሮኖችን በማምረት ለዓለም ገበያ የማቅረብ ራዕይ ሰንቆ እየተንቀሳቀሰ የሚገኝ ሲሆን፤ ከዚህ ቀደምም ከተለያዩ ተቋማት ጋር በትብብር ለመስራት ስምምነት ፈጽሟል።
በኢትዮጵያ ቁልፍ የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ላይ የሚቃጡ የሳይበር ጥቃቶችን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም ተገንብቷል
Oct 14, 2025 192
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ቁልፍ የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ላይ የሚቃጡ የሳይበር ጥቃቶችን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም መገንባቱን የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ ገለጹ፡፡ የአስተዳደሩ ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ተቀርፆ ተግባራዊ ተደረጓል። ስትራቴጂው ዲጂታላይዜሽን፣ ዘመናዊ አገልግሎት አሰጣጥ አና ቴክኖሎጂን ማዕከል ያደረገ በመሆኑ በሁሉም መስኮች ገቢራዊ እንዲሆን በትኩረት መሰራቱን ገልጸዋል፡፡ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ዜጎች በቴክኖሎጂ ላይ ያላቸውን አረዳድ በማሳደግ ለዲጂታል መስፋፋት ዕድል ፈጥሯል ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ ከቴክኖሎጂ መስፋፋት ጋር ተያይዞ የሳይበር ጥቃት ይዘቱንና አይነቱን እየቀያየረ እየተከሰተ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ በዚህም የሳይበር ጥቃትን ቀድሞ መከላከል የሚያስችል አቅም መገንባት በሚያስችል የወትሮ ዝግጁነት የአሰራር ሥርዓት የቁጥጥርና ምላሽ መስጫ ማዕከላትን በማቋቋም ሁልጊዜም በተጠንቀቅ እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ ማዕከላቱን በቴክኖሎጂና በብቁ የሰው ኃይል በማሟላት የቅድመ መከላከልና ዓለም አቀፍ የቁጥጥር ስርዓት በመዘርጋት ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል፡፡ አስተዳደሩ በጥናት የተደገፈ የህግ ማዕቀፍ በማዘጋጀት፣ ፖሊሲና ስትራቴጂ በመቅረጽ በቴክኖሎጂ የተደገፈ የአሰራር ሥርዓት ዘርግቷል ብለዋል፡፡ ባለፈው ዓመት ዘመኑን የዋጀ አዲስ የሳይበር ደህንነት ፖሊሲ መጽደቁን ገልጸው፤ ፖሊሲው ዲጂታላይዜሽንን ከማስረጽ ባሻገር የሳይበር ጥቃትን ለመከላከል ተደራሽነትን ማስፋት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በታዳጊዎች የሰመር ካምፕ የሳይበር ታለንት ማዕከል የሚሰጠው ትምህርት፣ ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር የሚሰሩ የጥናትና ምርምር ስራዎች የዜጎችን ግንዛቤ በማሳደግ ገንቢ ሚና እየተወጡ እንደሚገኙም ገልጸዋል፡፡