ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ከዲጂታል ፐብሊክ መሰረተ ልማት አንጻር በሦስት ጉዳዮች ላይ በትኩረት መሥራት ይጠበቃል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Dec 21, 2025 46
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 12/2018(ኢዜአ)፡- ከዲጂታል ፐብሊክ መሰረተ ልማት (ኢንፍራስትራክቸር) አንጻር በሦስት ጉዳዮች ላይ በትኩረት መሥራት እንደሚጠበቅ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ማጠቃለያ እና የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ይፋዊ የማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት ላይ ገለጻ አድርገዋል። በገለጻቸውም፤ የዲጂታል መሠረተ ልማትን በሚመለከት ዲጂታል ፐብሊክ መሰረተ ልማት(ዲፒአይ) እና ኪ ፐብሊክ ኢንፍራስትራክቸር(ኬፒአይ) በሚል በሁለት ተከፍሎ እንደሚታይ ጠቁመዋል። አሁን እኛ የምናተኩረው ዲጂታል ፐብሊክ ኢንፍራስትራክቸር (ዲፒአይ) ላይ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፤ ከእነዚህ መካከል ዋና ዋና ተብለው የሚገለጹት ፋይዳ፣ ዲጂታል የክፍያ ሥርዓት እና ዳታ ኤክስቼንጅ መሆናቸውን አብራርተዋል። በተቋማትና በሌሎችም መካከል መረጃን ማስተሳሰር (ዳታ ኤክስቼንጅን) ካላረጋገጥን የምናስበውን የተሟላ ሥርዓት አንፈጥርም ሲሉ አስገንዝበዋል። በዚህ አግባብ እያንዳንዱ ተቋም እና ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ማየት ያለበት ሲስተም አለኝ ወይስ የለኝም ሳይሆን ሲስተሜ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የተደገፈ ነው ወይ የሚለውን ነው ሲሉም ገልጸዋል። በኤ አይ ካልተደገፉ የዲጂታል ኢንፍራስትራክቸሮቻችን እያሉ እንደሌሉ ይሆናሉ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በገለጻቸው። ስለሆነም ይህ እንዳይሆን የፋይዳን ጉዳይ አበክረን በመሥራት መቶ በመቶ ማዳረስ ያስፈልጋል ብለዋል። በተጨማሪም የክፍያ ሥርዓቶቻችን የሚናበቡ መሆን አለባቸው፤ በባንኮች መካከል፣ በመንግሥት ተቋማት መካከል፣ በመንግሥትና በግል የተለየ ዳታ ሌየር መካከል የዳታ ኤክስቼንጅ ማድረግ ያስፈልጋል ነው ያሉት። እነዚህን ማከናወን ካልተቻለ ግን ዲጂታል የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ የሚያግዝ መሆን አይችልም፤ ማኑዋል የነበረውን ነገር በኮምፒውተር ማድረግ ብቻም በቂ አይደለም ሲሉ አስገንዝበዋል። #DigitalEthiopia2030
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ሙሉ በሙሉ ስኬታማ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Dec 21, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 12/2018(ኢዜአ)፡- ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ መቶ በመቶ በሚባል ደረጃ የተሳካ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ማጠናቂቀያ እና በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በይፋ የማስመጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በገለጻቸውም፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ሲነደፍ በዲጂታል ሴክተር ስትራቴጂ አውጥቶ የመተግበር ልምድ ብዙም ስላልነበረን አይሳካም የሚል ፍራቻ እንደነበር አውስተዋል። ይሁን እንጂ በሚያስደንቅ ሁኔታ ከአምሥት ዋና ዋና ዘርፎች መካከል አንዱ ስትራቴጂ መሆን አለበት ለኢትዮጵያ ብልጽግና አይተኬ ሚና አለው ከሚለው ውሳኔ ጀምሮ የተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት ዲጂታልን ከግብርና፣ ከኢንዱስትሪ፣ ከቱሪዝም እና ከማዕድን አስተካክሎ የማየት ዕይታ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ ኋላም ስትራቴጂው ተነድፎ የተተገበረበትን መንገድ ስንመለከት በግብርና፣ በማዕድን ብሎም በኢንዱስትሪው እንደተገኘው ስኬት በዲጂታሉ ዘርፍም ተገኝቷል ብለዋል። በመሆኑም የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ መቶ በመቶ በሚባል ደረጃ የተሳካ ስትራቴጂ ነው ሲሉ ገልጸዋል። ይህን ስትራቴጂ በመንግሥት መዋቅር ብቻ ሳይሆን አካዳሚውም እንዲፈትሸው እጋብዛለሁ ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው። ስትራቴጂው ምን ነበር ትልሙ(ንድፉ)?፣ ምን ተሳካ?፣ ምን አልተሳካም? የሚለው ሲታይ፤ አንድን ነገር አርቆ ማለም(ማቀድ) ብቻ ሳይሆን የመከወን ብቃት ከዚያ ውስጥ እንዴት ሊወጣ እንደሚችል ያመላከተ አስተማሪ ጉዞ ነበርም ነው ያሉት። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መንደርደሪያ ያደረገውም የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን መሆኑን ጨምረው አስታውቀዋል። #DigitalEthiopia2030
የግሉን ዘርፍ እና ስታርታፕን በማበረታታት የዳታ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ይገባል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Dec 21, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 12/2018(ኢዜአ)፡- የግሉን ዘርፍ በተለይም ስታርታፕን በማበረታታት የዳታ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ይገባል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ማጠቃለያ እና በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 በይፋ የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ ገለጻ አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ገለጻ፤ ሉዓላዊነት በየዘመኑ ካለ ጉዳይ ጋር እያደገ የሚሄድ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ ከዛሬ 100 ዓመታት በፊት ሉዓላዊነት ከድንበር ማስከበር ጋር የተያያዘ ሃሳብ እንደነበር አስታውሰው አሁን ላይ በራሳቸው ምግባቸውንና ሃሳባቸውን የማያመርቱ ሀገራት ስለ ሉዓላዊነት ሊያወሩ እንደማይችሉ ገልጸዋል፡፡ አሁን ባለንበት በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዘመን ሉዓላዊነት ዳታ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዳታን መቆጣጠር እና ከሀገራት ፈቃድና ፍላጎት ውጪ ሌሎች እንዳይጠቀሙበት ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ አህጉራችን አፍሪካ የሁሉም ቴክኖሎጂ ግብዓቶች መገኛ ብትሆንም ከሌሎች ሀገራት በምታስገባቸው ቺፕስን የመሰሉ የቴክኖሎጂ ግብዓቶች ምክንያት የዳታ ሉዓላዊነትን ማስጠበቅ አለመቻሏን አንስተዋል፡፡ በአፍሪካ ጥቂት የማይባሉ ሀገራት ሲስተሞቻቸውን ከሌሎች ሀገራት በማምጣት የሚጠቀሙ በመሆኑ ከሀገራት ጋር በሚፈጠሩ አለመግባባቶች የሲስተም መዘጋት ሲያጋጥምና ይህም የሀገራትን እንቅስቃሴ ሲያግድ ይስተዋላል ነው ያሉት፡፡ ይህንን ለመቅረፍ የአፍሪካን አቅም ለመጠቀም እንቅስቃሴ መጀመሩንና ለዚህም በኢትዮጵያ የተጀመረውን የፋይዳ እና ቴሌብር ቴክኖሎጂ ለተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ገበያ ለማቅረብ ድርድር መጀመሩን ለማሳያነት አንስተዋል፡፡ የዳታ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ሀገር በቀል የግል ኩባንያዎችና ስታርታፖች በአፍሪካ ገበያ እንዲወዳደሩ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑንም አስገንዝበዋል። የዳታ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ሀገር በቀል የግል ኩባንያዎች እና ስታርታፖች በአፍሪካ ገበያ እንዲወዳደሩ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑንም አስገንዝበዋል። በዚህም የዳታ ሉዓላዊነትን ማስጠበቅ ብቻ ሳይሆን የሌላውን የመጠቀም አቅማችን እያደገ ይሄዳል ብለዋል ነው ያሉት፡፡ በመሆኑም ተቋማትና ኃላፊዎች የግሉን ሴክተር በተለይም ስታርታፖችን በቴክኒክ፣ በገንዘብ እና የገበያ እድል በማመቻቸት መደገፍና ወደ ገበያ ገብተው ትርፋማ እንዲሆኑ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል ብለዋል፡፡ #DigitalEthiopia2030
በፈጠራ ሥራው ለብዙኃን ብርሃን የፈነጠቀው ወጣት 
Dec 21, 2025 155
ብዙዎች ችግርን ሲያማርሩ ጥቂቶች ግን ችግርን ወደ ዕድል ይቀይሩታል። ወጣት ፌደሳ ሹማ ከእነዚህ ጥቂት ባለ ራዕይ ወጣቶች መካከል አንዱ ነው፡፡ ወጣቱ በኢትዮጵያ የተሰራ በሚል ስም ድምጽና ጭስ አልባ ዘመናዊ ጄነሬተሮችን የሚያመርተው "ፌዶ ፓወር ሶሉሽን" (Fedo Power Solution) ባለቤት ነው፡፡ የወጣቱ የጥረትና የፈጠራ ውጤት ዘመናዊና ለአካባቢ ተስማሚ ጄኔሬተር ሲሆን፤ ወጣት ፌዴሳ ምርቱን ለዓለም ገበያ ለማቅረብ ሕልም ሰንቋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ወጣቶች በሰመር ካምፕ የሰሯቸውን የፈጠራ ቴክኖሎጂዎች በተመለከቱበት ወቅት፤ ሀገር የምትሻገረው ከትንሽ ተነስተው ወደ ትልቅ ኩባንያዎች በሚያድጉ ስራ ፈጣሪ ወጣቶች እንደሆነ መናገራቸው ይታወሳል፡፡ የፈጠራ ስራዎቹ ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት እንደሚጥሉ ጠቅሰው፤ የተመለከቱት ጄኔሬተር አንድ ጊዜ ቻርጅ ተደረጎ ተጨማሪ ነዳጅ ሳይጠቀም ለበርካታ ሰዎች ብርሃን መስጠት የሚያስችል ድንቅ የፈጠራ ስራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ እንዲህ ያሉ የፈጠራ ስራዎች ኢትዮጵያውያንን ወደ ተሻለ አኗኗር የሚያሸጋግሩ ናቸው ነው ያሉት፡፡   የፌዶ ፓወር ሶሉሽን መስራች ወጣት ፌደሳ ሹማ ከኢዜአ ጋር ባደረገው ቆይታ እንደገለጸው፤ የፈጠራ ስራውን የጀመረው በአካባቢው በተደጋጋሚ የሚከሰተው የኤሌክትሪክ መቆራረጥ በስራው ላይ በፈጠረበት ተግዳሮት የተነሳ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ለስራው ይጠቀምበት የነበረው ጄኔሬተር ነዳጅ የሚጨርስ፣ ድምፁ የሚረብሽና ጭስ የሚያወጣ መሆኑ ለወጣቱ ትልቅ ራስ ምታት ሆኖበት እንደነበርም ያስታውሳል፡፡ ይህንኑ ችግር ለማቃለል መፍትሄ መፈለግ የጀመረው ወጣት ፌደሳ በ2014 ዓ.ም የራሱን ጄኔሬተር በመሥራት የፈጠራ ሕልሙን ዕውን ማድረጉን ተናግሯል፡፡ ወጣቱ በፈጠራ ሥራው ለመጀመሪያ ጊዜ በደምቢ ዶሎ ዩኒቨርሲቲ በተዘጋጀ ውድድር አሸናፊ በመሆን የፈጠራ አቅሙን መረዳት እንደቻለ ያስታውሳል፡፡ ከዛም በዞን፣ በክልልና በፌዴራል ደረጃ የተደረጉ የፈጠራ ውድድሮችን በማሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ የ260 ሺህ ብር የገንዘብ ሽልማት ማግኘቱ ለስራው ማደግ የራሱ ሚና እንደነበረው ጠቅሷል፡፡ ይህ ሽልማት ለትልቅ ሕልሙ መነሻ እንደሆነው የሚናገረው ወጣት ፌደሳ፤ መጀመሪያ በ300 ኪሎ ዋት የጀመረው የፈጠራ ሥራ ዛሬ ወደ 600 እና አንድ ነጥብ አምስት ሜጋ ዋት መሸጋገሩንም ተናግሯል፡፡ ፌዶ ፓወር ሶሉሽን የሚያመርታቸው ጄኔሬተሮች ድምፅና ጭስ አልባ መሆናቸው ለአካባቢ ጥበቃና ለጤና ተስማሚ አድርጓቸዋል። ጄኔሬተሩ በኤሌክትሪክም ሆነ በሶላር(በፀሐይ ኃይል) ቻርጅ መስራት የሚችል ሲሆን፤ ወጪ ቆጣቢና በአንድ ጊዜ ቻርጅ ረጅም ጊዜ የሚያገለግልና ለማንኛውም ተቋም የሚመጥን ነው ብሏል። በአሁኑ ወቅት ፌዶ ፓወር ከ60 በላይ ለሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩንና በቀን የተለያየ አቅም ያላቸውን 100 ጄኔሬተሮች ለማምረት እየሠራ እንደሚገኝም አንስቷል፡፡ የሰነቅኩት ሕልም በዚህ አያበቃም የሚለው ወጣቱ "በኢትዮጵያ የተመረተ" የሚል ታሪካዊ አሻራ ያረፈባቸውን ምርቶች ወደ አፍሪካና ወደ ተለያዩ የዓለም ሀገራት የመላክ ትልቅ ራዕይ መሰነቁንም ይናገራል፡፡ ወጣት ፌደሳ ሹማ በመንግሥት እየተደረገለት ላለው ድጋፍ አመስግኖ፤ ወጣቶች የጀመሩትን የፈጠራ ሥራ ተስፋ ሳይቆርጡ እንዲገፉበትና ሕልማቸውን ዕውን ለማድረግ እንዲተጉ ጥሪውን አስተላልፏል። የሀገር ዕድገት የሚረጋገጠው በፈጠራና በዕውቀት ሽግግር ነው የሚለው ወጣቱ፤ የኢኖቬተሮች ሚና ለኢትዮጵያ ብልጽግና ወሳኝ መሆኑን አጽንኦት ሰጥቷል።   የፌዶ ፓወር ሶሉሽን ቺፍ ቴክኒሽያን ኦፊሰር ሄኖክ አማኑኤል በበኩሉ፤ ድርጅቱ የሚያመርታቸው ጄኔሬተሮች ዋነኛ የኃይል አማራጭ መሆን መጀመራቸውን ጠቁሟል፡፡ ድርጅቱ የሚያመርታቸው ጄኔሬተሮች ለሆስፒታሎች፣ ለትምህርት ቤቶች፣ ለመንግስትና ለግል ተቋማት ጥቅም መስጠት እንደሚችል ጠቅሷል፡፡   በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የስታርታፕና ኢኖቬቲቭ ኢንተርፕራይዞች ድጋፍ ዴስክ ኃላፊ ሙሉጌታ ውቤ፤ በኢትዮጵያ የስታርታፕ ስነ-ምህዳሩ በከፍተኛ ሁኔታ መነቃቃት እያሳየ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡ ሚኒስቴሩ ስታርታፖችን ለመደገፍ ስታርታፕ ኢትዮጵያ እና ስትራይድ ኢትዮጵያ የተባሉ ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት አቅማቸውን እንዲያሳዩና ትስስር እንዲፈጥሩ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ስታርታፖች ወደ ኢንኩቤሽን ማዕከላት ገብተው ስራዎቻቸውን እንዲያበለጽጉና በዓለም አቀፍ ደረጃ የፈጠራ ስራዎቻቸውን እንዲያሳዩ ዕድል መፈጠሩንም ተናግረዋል፡፡ ስታርታፖች የፈጠራ ስራዎቻቸውን አሳድገው ወደ ምርት እንዲገቡ እገዛ እየተደረገ መሆኑን አስታውሰው፤ ከሁለት ሺህ በላይ ለሚሆኑ የፈጠራ ባለሙያዎች ድጋፍ መደረጉንም ጠቅሰዋል፡፡ የስታርታፕ የፈጠራ ውጤቶች የዜጎችን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ በማሳለጥ በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛሉ፡፡
የዲጂታል መሰረተ ልማት መስፋፋት የከተሞችን ምጣኔ ሃብታዊ እና ማህበራዊ እድገት እያፋጠነ ነው
Dec 21, 2025 100
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 12/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት የዲጂታል መሰረተ ልማትን በመገንባት እና በማስፋፋት የከተሞችን ምጣኔ ሃብታዊና ማህበራዊ እድገት እያፋጠነ እንደሚገኝ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ገለፀ። መንግስት በኢትዮጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ማሳካት የሚያስችሉ መሰረታዊ መደላድሎችን ለመፍጠር በርካታ ስራዎች እያከናወነ ይገኛል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ የከተሞች ሁለንተናዊ እድገት እውን የሚሆነው የአሰራር ስርዓትን በቴክኖሎጂ ማስደገፍ ሲቻል ነው። ሚኒስቴሩ የከተሞችን አገልግሎት አሰጣጥ በቴክኖሎጂ በማስደገፍ ቀልጣፋና ፍትሐዊ አገልግሎት እንዲሰጡ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። መንግስት የዲጂታል መሰረተ ልማትን በመገንባት እና በማስፋፋት የከተሞችን ምጣኔ ሃብታዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ እድገት እያፋጠነ እንደሚገኝ ነው ያብራሩት። በዚህም ዜጎች ያለምንም መጉላላት ጉዳያቸውን በቀላሉ ማስፈፀም የሚችሉባቸውን አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች የማስተዋወቅና የማላመድ ስራዎች መከናወናቸውንም አንስተዋል። ከተሞች ለነዋሪዎቻቸው የሚሰጡትን አገልግሎቶች ምቹና ቀልጣፋ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አመርቂ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ሚኒስትር ዴኤታው ተናግረዋል። በቅርቡም በአዲስ አበባ፣ አዳማ፣ ቢሾፍቱ፣ ሃዋሳና ሌሎች ከተሞች የኦን ላይን አገልግሎት በስፋት መጀመሩን ገልፀው፤ በቀጣይ በተለያዩ ከተሞች አገልግሎቱ ተደራሽ እንደሚደረግ አስታውቀዋል። ዜጎች ሁሉንም አገልግሎቶች በአንድ ቦታ የሚያገኙበት መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎች በሁሉም ክልሎች እየተገነቡ እንደሚገኙ ገልፀዋል። ማዕከሉ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የተለያዩ የመንግስት አገልግሎቶችን በማጣመር በአንድ ጣራ ስር የሚሰጥበት መሆኑን ጠቅሰዋል። በዚህም የሚሰጡ አገልግሎቶች ጥራት ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻል እያሳየ መምጣቱንም ነው ሚኒስትር ዴኤታው ጨምረው የተናገሩት። ሚኒስቴሩ በ2018 በጀት ዓመት የከተሞችን አገልግሎት አሰጣጥ የሚያቀላጥፍ አዲስ ሶፍትዌር በማበልፀግ በሁሉም ከተሞች ስራ ለማስጀመር ዝግጅት ማጠናቀቁንም አስታውቀዋል።
በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ በሳይበር ደህንነት ላይ በርካታ አስቻይ መሰረቶች ተጥለዋል
Dec 20, 2025 110
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦ በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ በሳይበር ደህንነት ላይ በርካታ አስቻይ መሰረቶች ተጥለዋል ሲሉ የኢንፎርሜሽንና መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በመድረኩ የኢንፎርሜሽንና መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሀሚድ በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ በሳይበር ደህንነት ላይ በርካታ አስቻይ መሰረቶች ተጥለዋል ነው ያሉት። በዚህም የራሳችንን ክላውድ መሰረተ ልማት በመገንባት በኢትዮጵያ የዲጂታል አገልግሎት መተማመን መፍጠር ተችሏል ብለዋል። ለጸጥታ ተቋማትም የዲጂታል ፎረንሲክ ላብ በመገንባት ወደ ስራ እንዲገባ መደረጉንም ጨምረው ገልጸዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የሳይበር ደህንነት ስትራቴጂካዊ ትኩረት ተሰጥቶታል ሲሉም ዋና ዳይሬክተሯ ተናግረዋል። በዚህም የማይበገር ቁልፍ የዲጂታል መሰረተ ልማት መገንባት፣ የህዝብ መሰረተ ልማትን ማዘመን፣ የአደጋ ምላሽ መስጫ ማዕከል የማቋቋምና የግል ተቋማትን ያካተተ የሳይበር ደህንነት ስራ እንዲጎለብት ይሰራል ብለዋል።
ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ ላይ ቁልፍ ጉዳይ ሆኖ ተተግብሯል።
Dec 20, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ ላይ ቁልፍ ጉዳይ ሆኖ ተተግብሯል ሲሉ የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና አስተባባሪ ዮዳሄ አርአያስለሴ አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በመድረኩ የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና አስተባባሪ ዮዳሄ አርአያስለሴ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ ላይ ቁልፍ ጉዳይ ሆኖ ተተግብሯል ብለዋል። አሁን ላይ 30 ሚሊዮን ዜጎች ፋይዳ መታወቂያ ተመዝግበዋል ሲሉም ጨምረው ገልጸዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ላይ ፋይዳ ስትራቴጂካዊ ትኩረት የተሰጠው ሲሆን ሙሉ ለሙሉ ተደራሽ የማድረግ ስራም ይሰራል ነው ያሉት። በተለይ እስከታችኛው መዋቅር ድረስ ያሉ አገልግሎቶችን ከፋይዳ ጋር በማስተሳሰር በስትራቴጂው የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት በትኩረት ይሰራል ብለዋል። ለዚህ ደግሞ ሁሉም በትብብር ሊሰራ እንደሚገባ አቶ ዮዳሄ አርአያስለሴ አስገንዝበዋል።
በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ስነ ምህዳር ማስፋት የሚያስችሉ በርካታ ስራዎች ይከናወናሉ
Dec 20, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ስነ ምህዳር ማስፋት የሚያስችሉ በርካታ ስራዎች ይከናወናሉ ሲሉ የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር) በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ስነ ምህዳር ማስፋት የሚያስችሉ በርካታ ስራዎች ይከናወናሉ ብለዋል። የራሳችንን ክላውድ ከመጠቀም ባሻገር ውጤታማ የመረጃ አስተዳደር ስርዓት እንዲኖር ይደረጋል ሲሉም ገልጸዋል። በዚህም በተደራጀ አግባብ መረጃዎች ለወሳኔ አሰጣጥ እንዲውሉ የሚሰራ ሲሆን፣ ከዚህ ጋር በተያያዘ ገለልተኛ ብሔራዊ የመረጃ ባለስልጣን ወደ ስራ እንዲገባ ይደረጋል ነወ ያሉት። ዲጂታል አገልግሎት አሰጣጦችን የማናበብንና ወጥ የማድረግ ስራ ላይም ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በሲቪል ምዝገባና የዜግነት አገልግሎት ተደራሽነት ላይ ትልቅ ለውጥ አምጥቷል
Dec 20, 2025 73
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በሲቪል ምዝገባና የዜግነት አገልግሎት ተደራሽነት ላይ ትልቅ ለውጥ አምጥቷል ሲሉ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ታዬ ግርማ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በመድረኩ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ታዬ ግርማ እንዳሉት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በሲቪል ምዝገባና የዜግነት አገልግሎት ተደራሽነት ላይ ትልቅ ለውጥ አምጥቷል አክለውም አግልግሎቱን ከተለያዩ ተቋማት ጋር በማስተሳሰር ረገድም ትልቅ ተሞክሮ የሚሆን ስራ ተከናወኗል ብለዋል። ለአብነትም በአዲስ አበባ ከማዕከል እስከ ወረዳ ትስስር መፍጠር የተቻለ ሲሆን፣ ለስራው የሚያገለግሉ መተግበሪያዎችም በሀገር ውስጥ አቅም የለሙ ናቸው ሲሉም ተናግረዋል። በዚህም የቤተሰብ ምዝገባ፣ ወሳኝ ኩነት፣የነዋሪዎች አገልግሎትና የማረጋገጥ ስራዎች በዲጂታል ስርዓት ተግባራዊ እየተደረጉ ነው ብለዋል። ይህም በ2030 ተቋማት በዲጂታል አሰራርና በመረጃ የተሳሰሩ እንዲሆኑ ለሚከናወነው ስራ ተሞክሮ መሆን የሚችል ነው ሲሉ ገልጸዋል።
ስታርት አፕና የዲጂታል ክህሎት ልማት ለዲጂታል 2030 ስትራቴጂ መሳካት ትልቅ ሚና ከሚጫወቱ ጉዳዮች መካከል ተጠቃሾች ናቸው።
Dec 20, 2025 52
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦ ስታርት አፕና የዲጂታል ክህሎት ልማት ለዲጂታል 2030 ስትራቴጂ መሳካት ትልቅ ሚና ከሚጫወቱ ጉዳዮች መካከል ተጠቃሾች መሆናቸውን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ደኤታ ሙሉቀን ቀሬ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በመድረኩ ላይ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ደኤታ ሙሉቀን ቀሬ በተለይ የዲጂታል ክህሎትን ለማሳደግ ወሳኝ አቀጣጫዎች ተቀምጠዋል ብለዋል። በዚህም በ2030 ከሀገሪቱ አጠቃላይ ህዝብ 70 በመቶ የሚሆነው የዲጂታል እውቀት እንዲኖረው፣ 80 በመቶ የሚሆነው የመንግስት ሰራተኛ የዲጂታል ክህሎት የተላበሰ እንዲሆን፣ 10 ሚሊዮን ዜጎች የዲጂታል ስልጠና እንዲወስዱ በልዩ ትኩረት የሚሰራ ይሆናል ነው ያሉት። ከዚህ በተጨማሪ 5 ሺህ ስታርት አፖች ወደ ስራ እንዲገቡና በዲጂታል ዘርፍ ለ1 ሚሊዮን ዜጎች የስራ እድል እንዲፈጠርም እንደሚሰራ ተናግረዋል። በሌላ በኩል በ2030 ከሀገር ወስጥ አጠቃላይ ምርት ዲጂታል ዘርፍ ገቢ 12 በመቶ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም ጨመረው ገልጸዋል።
ዲጂታላይዜሽን የብልጽግና ግብ ማሳኪያ ቁልፍ መሳሪያ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Dec 20, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት የዲጂታል ዘርፉን ተደራሽነት በማስፋት የብልጽግና ግብ ማሳኪያ ቁልፍ መሳሪያ አድርጎ እየሰራበት መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የብሔራዊ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ምክር ቤት ሊቀ መንበር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና ብሔራዊ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ምክር ቤት ሊቀ መንበር ተመስገን ጥሩነህ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የማደግ ፍላጎትና አቅም ያላት ሀገር ናት። የኢትዮጵያ ዲጂታል መርሃ ግብርም በፈጠራና ፍጥነት እመርታን በማምጣት የማደግ ፍላጎትን ከአቅም ጋር እንዲናበብ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የለውጡ መንግስት የዲጂታል ዘርፍ እንደአስቻይ አቅም ብቻ የሚታይበትን የቀደመ እይታ ከፍ ማድረጉን ጠቅሰው፤ ዘርፉን ለሁሉም መስክ ተደራሽ በማድረግ አንደኛው የኢኮኖሚ አንቀሳቃሽና የብልጽግና መዳረሻ ግብን በእጅጉ ለማቅረብ በትኩረት እየተሰራበት ይገኛል ብለዋል። ከአምስት ዓመታት በፊት መተግበር የተጀመረው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂም የዲጂታል መሠረቶችን በማስቀመጥ ዘርፈ ብዙ የሪፎርም ሥራዎችን ለማከናወን ገንቢ ሚና መጫወቱን አስረድተዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የዲጂታል መሰረተ ልማቶችን በማስፋት ዘርፈ ብዙ ትሩፋት ማስገኘቱንም ነው የተናገሩት። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ትግበራ በመንግስት አሰራር፣ በአገልግሎት አሰጣጥ፣ በቴሌኮም ዘርፍ፣ በኃይል አቅርቦትና በፋይናንስ ተደራሽነት ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ማሸጋገሩን ገልጸዋል።   በተለይም የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ውጥኖችን የሚያግዙ የፋይናንስ፣ የሰው ሀብት ልማትና ፖሊሲ ትግበራ አቅምን ማሳደግ የሚሹ ሦስት ጉዳዮች ላይ አመርቂ ውጤት ማምጣቱን አስረድተዋል፡፡ በዚህም ኢትዮጵያን ወደ ዲጂታል 2030 ማሸጋገር ያስቻለ አመርቂ ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን አንስተዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ሁሉን አቀፍና አካታች የዲጂታል አገልግሎቶችን በማቅረብና የውስጥ ፈጠራን በማበረታታት ሙሉ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ለማምጣት ቁልፍ ሚና እንደሚኖረው አስገንዝበዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት ከተለመዱ ተፈጥሯዊ አካሄዶች ባለፈ የመፍጠን፣ መዝለልና የፈጠራ ማዕከሎችን በመያዝ በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግ ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ ዘላቂ ልማት ታሳቢነት የተቀረጸው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂም የመንግስትን ልዩ ትኩረት ብቻ ሳይሆን የሁሉንም ባለድርሻ አካላትና የማኅበረሰቡን ተሳትፎ የሚጠይቅ ነው ብለዋል፡፡
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ተደራሽ፣ ፍትሃዊ እና አስተማማኝ የዲጂታል ምህዳር መፍጠር ላይ ትኩረት ያደረገ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Dec 20, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ተደራሽ፣ ፍትሃዊ እና አስተማማኝ የዲጂታል ምህዳር መፍጠር ላይ ትኩረት ያደረገ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ተሳክቷል። በተለይም በህዝብ መገልገያ ዲጂታል መሰረተ ልማቶች ዝርጋታ ውጤታማ ስራ መከናወኑን አንስተዋል። ለአብነትም ኢትዮጵያ ወሳኝ በሚባል ደረጃ ከጥሬ ገንዘብ ግብይት ወደ ዲጂታል የፋይናንስ ስርዓት መሸጋገሯን ጠቅሰው፤ በዚህም ገንዘብ ለማሳተም የሚወጣውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ማስቀረት መቻሉን አብራርተዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ም ባለፉት አምስት ዓመታት የተከናወኑ ተግባራትን መሰረት በማድረግ መዘጋጀቱን አንስተዋል።   ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ሦስት ቁልፍ ትልሞች እንዳሉት የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ እነዚህም ተደራሽነትን ማስፋት፤ እኩል እድል ማመቻቸትና በተቋማትና ህዝብ መካከል መተማመንን መፍጠር መሆናቸውን አብራርተዋል። እነዚህን ትልሞች ለማሳካት ደግሞ በሀገር አቀፍ ደረጃ የኤሌክትሪክና የቴሌኮም ትስስር ሙሉ ለሙሉ ተደራሽ መሆን እንዳለበት አስገንዝበዋል። ይህም እድገትን ከማሳለጥ ባሻገር በየአካባቢው ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር እንደሚያግዝ ተናግረዋል። ከዚህ አኳያ ስትራቴጂው ለህዝብ መገልገያ ዲጂታል መሰረተ ልማት መስፋፋት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራም ጠቁመዋል። በሌላ በኩል በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት የሚከናወኑ ሥራዎች በጠንካራ የሳይበር ደህንነት ሊታገዙ እንደሚገባም ተናግረዋል።   በዚህ ረገድ አበረታች ሥራ መከናወኑን አንስተው፤ አሁን ላይ በኢትዮጵያ ጠንካራ የሳይበር ደህንነት ተቋም ተገንብቷል ብለዋል። የሳይበር ደህንነት ሥራውም የዲጂታል ስርዓት፣ የዲጂታል መረጃንና ትውልዱን መጠበቅ እንዳለበትም ነው ያስገነዘቡት። በተለይ የትውልዱ የዲጂታል አጠቃቀም ከኢትዮጵያ ባህል፣ እሴትና ሉዓላዊነት ጋር በተናበበ መልኩ ሊሆን እንደሚገባ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያነሱት። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 እንዲሳካም ሁሉም በትብብር መስራት እንዳለበት ነው ጥሪ ያቀረቡት።
የሀገራችንን ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግረውን ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የትግበራ ምዕራፍ ዛሬ በይፋ አስጀምረናል-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Dec 20, 2025 71
ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁለንተናዊ የብልፅግና ጉዞ ለማፋጠን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ምርጫ ሳይሆን ግዴታችን ነው። ላለፉት አምስት ዓመታት ስንተገብረው የቆየነው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ሀገራችንን በቴክኖሎጂ የታገዘ የኢኮኖሚ መሠረት ላይ ለማቆም ያስቻሉ ተጨባጭ ውጤቶችን አስመዝግቧል። ከተመዘገቡ ዋና ዋና ስኬቶች መካከልም የዲጂታል መሠረተ ልማት፣ የሳይበር ምህዳር ደህንነት፣ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ፣ ዲጂታል ፋይናንስና ክፍያ፣ የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ዲጂታል ክህሎት የተላበሰ ብቁ ዜጋ መፍጠር ተጠቃሽ ናቸው።   አዲሱ ስትራቴጂ በተቀናጀ አመራርና በጠንካራ መዋቅር የሚመራ ሀገራዊ ስትራቴጂ ነው። ስትራተጂው ሁሉን አቀፍና አካታች የዲጂታል አገልግሎቶችን ተደራሽ ያደርጋል፤ ዜጎችን ማዕከል ያደረገ ዲጂታል መንግሥት ይገነባል፤ የሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችንና ስታርታፖችን ያበረታታል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስኬት ከተለመደው አካሄድ ወጥተን፣ በፈጠራና በፍጥነት የታጀበ የዲጂታል ዝላይ ጉዞ ማድረግን ይጠይቃል። ለዚህ ደግሞ የመንግሥት ተቋማትና የግሉ ዘርፍ አገልግሎታቸውን ይበልጥ በማዘመን፣ የልማት አጋሮች ድጋፋቸውን ከስትራቴጂያችን ጋር በማጣጣም፣ ወጣቶችና ባለሙያዎች በፈጠራ አቅማቸው ሀገራዊ መፍትሔዎችን በማመንጨት፣ የድርሻቸውን እንዲወጡ አደራ እላለሁ። የኢትዮጵያን ብልፅግና በዲጂታል እውቀትና ፈጠራ እናሳካዋለን። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በይፋ አስጀመሩ 
Dec 20, 2025 68
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018 (ኢዜአ):- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ የታለመለትን ግብ አሳክቶ መጠናቀቁን ገልጸዋል። ዛሬ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 በይፋ መጀመሩን ጠቁመው፤ ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል እድል መፍጠር እንዲሁም በዜጎችና ተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት ደግሞ የስትራቴጂው ቁልፍ መሰረታዊ ትልሞች መሆናቸውን አመልክተዋል።   ትልሞቹ እንዲሳኩም በተለይ የህዝብ ዲጂታል መሠረተ ልማት ማስፋት ላይ ትልቅ ስራ እንደሚከናወን ጠቁመው፤ ይህም ዲጂታል ቴክኖሎጂ ሰው ተኮር ሆኖ የዜጎችን ኑሮ እንዲያሻሽል ትልቅ አቅም ይፈጥራል ብለዋል። በአጠቃላይ በዲጂታል ኢትዮጵያ የሚከናወኑ ስራዎች የመደመር መንግስት በቀለለ ቢሮክራሲ ታላላቅ ስትራቴጂዎችን እውን ለማድረግ ከያዘው ግብ ጋር የተሳሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የተሟላ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ እያስቻለን ነው
Dec 20, 2025 74
ወልቂጤ፤ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ መያዛችን የተሟላ፤ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ እያስቻለን ነው ሲሉ የወልቂጤ ከተማና አካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ። የዲጂታል ኢትዮጵያን እቅድ ለማሳካት እየተከናወኑ ከሚገኙ ተግባራት መካከል የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ አገልግሎትን ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። በዚህም መሰረት የፋይዳ መታወቂያን በመያዝ ዜጎች የሚፈልጉትን መንግስታዊና ማህበራዊ አገልግሎት ማግኘት ጀምረዋል። ከዚሁ ጋር በተገናኘ ኢዜአ ያነጋገራቸው የወልቂጤ ከተማና አካባቢው ነዋሪዎች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ መያዛችን የተሟላ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንድናገኝ እያስቻለን ነው ብለዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል ወይዘሮ በላይነሽ ገብሬ፤ የፋይዳ መታወቂያ በተደራጀ መልኩ የተፋጠነ አገልግሎት እንድናገኝ እያስቻለን ነው ሲሉ ተናግረዋል። የመታወቂያውን አስፈላጊነት በመረዳትም ከራሳቸው ባለፈ ከ5 ኣመት በላይ የሆኑ ልጆቻቸው የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ እንዲያወጡ ማድረጋቸውን ገልፀዋል። ሌላኛው አስተያየት ሰጭ አቶ መልስ ዶርጌ፤ የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ለአገልጋይም ሆነ ለተገልጋይ የተፋጠነ እና የተሟላ አገልግሎት ለመስጠት ወሳኝ ስለመሆኑ ተናግረዋል። በአካባቢው የሚኖሩት ወጣት ጥላሁን ሸዋረጋ እና ወጣት ታገሱ ደጉ፤ የፋይዳ መታወቂያ በመያዛቸው በተለያዩ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተቀላጠፈ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ገልጸዋል። የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ልዩ አማካሪ እና የፋይዳ ብሄራዊ መታወቂያ አገልግሎት ግብረ ሃይል አስተባባሪ ዳርጌ ተክሉ፤ በዞኑ እስካሁን በ58 ማእከላት 249 ሺህ 951 ዜጎች የፋይዳ ድጅታል መታወቂያ ተመዝግበው መውሰዳቸውን ተናግረዋል። በተያዘው በጀት አመትም 732 ሺህ 600 ዜጎች ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በአገልግሎት መስጫ ተቋማት ለዜጎች ፈጣንና የተቀላጠፈ አገልግሎት መስጠት እያስቻለ መሆኑን አንስተው፥ ሌሎችም መታወቂያውን በመያዝ የእድሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ መክረዋል።
የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በማስፋት የዜጎችን የአገልግሎት ፍላጎት ለማሟላት የተቀናጀ ጥረት ይደረጋል-ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ
Dec 20, 2025 95
ጅግጅጋ፤ታህሳስ 11/2018 (ኢዜአ)፦የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በማስፋት የዜጎችን የአገልግሎት ፍላጎት ለማሟላት የተቀናጀ ጥረት የሚደረግ መሆኑን የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ ገለጹ። በሶማሌ ክልል የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት የተጀመረ ሲሆን በማስጀመሪያ መርሐግብር ላይ ሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ ሙሁመድ እንዲሁም በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አክሊሉ ታደሰ እና ሌሎች የፌዴራል የክልሉ መንግስት የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ዛሬ አገልግሎት የጀመረው የጅግጅጋ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት የዜጎችን እንግልት በማስቀረት ፈጣን አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ማዕከሉ በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀልጣፋና ፈጣን አገልግሎት መስጠት የሚያስችል በመሆኑ ተጠያቂነትን ለማስፈንም እንደሚረዳ ተናግረዋል። ማዕከሉ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት በሚያስችል ዘመናዊ መሰረተ ልማት እና የሰው ሀይል የተሟላለት መሆኑንም አንስዋል። አገልግሎቱን ለማስፋፋትም በቀጣይ በክልሉ 13 ከተሞች መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ተግባራዊ ለማድረግ ይሰራል ብለዋል።   በመሆኑም የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በሌሎች ከተሞችም በማስፋት የዜጎችን የአገልግሎት ፍላጎት ለማሟላት የተቀናጀ ጥረት የሚደረግ መሆኑን ገልጸዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አክሊሉ ታደሰ በበኩላቸው፥ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ፣ ከአድሎ የጸዳ አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል።   የአንድ ማዕከል አገልግሎቱ መንግሥትና ህዝብን የበለጠ የሚያቀራርብ እንዲሁም ሰው ተኮር የአገልግሎት ልህቀትን ለማረጋገጥም የሚያግዝ መሆኑን አስረድተዋል። በአጠቃላይ ማዕከሉ መንግስት በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ የጀመረው ሪፎርም ለማሳካት ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑንም አብራርተዋል። ዛሬ አገልግሎት የጀመረው ማዕከሉ 9 ተቋማትን በውስጡ የያዘ ሲሆን 32 አገልግሎቶችን እንደሚሰጥ ተገልጿል።
ወልዲያ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ስራው በተጓዳኝ የማሕበረሰብ አገልግሎትን እያጠናከረ ነው
Dec 20, 2025 72
ወልዲያ ፤ ታሕሳስ 11/2017(ኢዜአ)፡- ወልዲያ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ስራው በተጓዳኝሕብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የማሕበረሰብ አገልግሎትን አጠናክሮ መቀጠሉን አስታወቀ ። በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ሽግግርና ማሕበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክተር አማረ ቢሆን (ዶ/ር )፤ ዩኒቨርስቲው አገልግሎቱን የሚሰጠው በወልዲያ፣ በሰሜን ወሎና በዋግ ኸምራ አካባቢዎች ነው። በዚህም ከመማር ማስተማር ስራው በተጓዳኝ በግብርና፣ በጤና፣ በትምሕርት፣ በከተሞች ዲዛይን ንድፍና በቴክኖሎጂ ማስፋፋት ላይ በማተኮር የማሕበረሰብ አገልግሎቱን እየሰጠ እንደሚገኝ አንስተዋል። በጤናው ዘርፍ 78 የዩኒቨርሲቲውን ባለሙያዎች በመመደብ በወልዲያ ስፔሻላይዝድ ጠቅላላ ሆስፒታል በቀዶ ሕክምና ላይ በነጻ እያገለገሉ መሆኑን ጠቅሰዋል። የወልዲያ ከተማን የወንዝ ዳር ልማትን ዘመናዊና ሳቢ ለማድረግ የዲዛይንና የከተማ አገልግሎቱን አሰራር በቴክኖሎጂ በማስደገፍ እንዲሰራ እገዛ ተደርጓል ብለዋል። በትምሕርት ዘርፉም የ12ኛ ክፍል ተማሪዎች በትምህርታቸው የተሻለ ውጤት እንዲያመጡ በቁሳቁስና በስልጠና በማገዝ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስረድተዋል። ዩኒቨርሲቲው ባከናወነው የማሕበረሰብ አገልግሎት ስራም ከ101 ሺህ በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በቀጥታና በተዘዋዋሪ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አውስተው፤ ተቋሙ የማሕበረሰብ አገልግሎቱ አጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቀዋል። ዩኒቨርሲቲው ባለሙያዎችን በመመደብ የነበረባቸውን የስራ ጫናና የመደራረብ ችግር በመፍታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል ያሉት ደግሞ የወልዲያ ስፔሻላይዝድ ጠቅላላ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ አቶ ፍስሃ የኋላው ናቸው። ወረፋ በመጠባበቅ ላይ የነበሩ የቀዶ ሕክምና የሚያስፈልጋቸውን ወገኖችን በዩኒቨርሲቲው እገዛ ሕክምና እንዲያገኙ ማድረጉን ጠቅሰዋል። የዩኒቨርሲቲ ድጋፍ ቀጥሎ እንዳለም አንስተዋል።   በሐብሩ ወረዳ የቁጥር 28 ቀበሌ ነዋሪ አቶ አሕመድ ሐሰን በሰጡት አስተያየት ፤ በፍየል እርባታ ስራ ብዙ ቢደክሙም የሚያገኙት ጥቅም አነስተኛ ሆኖ መቆየቱን አስታውሰዋል። በዩኒቨርሲቲው ባለሙያ እገዛ የተደረገላቸው የፍየል ዝርያ ማሻሻያ በአካል የገዘፉና የስጋ ምርታቸው ከፍተኛ የሆኑ በማርባት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል።  
ቴክኖሎጂው አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን ለማሳደግ የሚያስችል ነው
Dec 20, 2025 117
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን ለመተግበር ከህዋዌ ጋር በትብብር እንደሚሰራ አስታወቀ። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሚሰጠውን አገልግሎት በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግና ይበልጥ ለማዘመን የሚያስችለውን የመግባቢያ ስምምነት ከቻይናው ሁዋዌ ኩባንያ ጋር ተፈራርሟል፡፡ በዚህም፥ ስማርት ግሪድ ለማስፋፋት፣ የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ዝርጋታ ለማዘመንና አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን ከህዋዌ ጋር በትብብር ለመዘርጋት የሚያስችል መሆኑን ዋና ስራ አስፈፃሚ ኢንጅነር ጌቱ ገረመው በፊርማ ስነ ስርዓቱ ወቅት ተናግረዋል፡፡   ኢንጅነር ጌቱ አክለውም፥ በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሰረተ ልማትን ለማስፋፋት ሁለቱም ተቋማት በትብብር ለመስራት መስማማታቸውን ገልፀዋል፡፡ ዘመናዊ የኤሌክትሪክ መስመር ስርጭት መቆጣጠሪያ ለመገንባት፣ ለረጅም ጊዜ ኢነርጅ የሚያቆዩ ባትሪዎችን ለመትከልና የዘመኑ ቴክኖሎጂዎችን በኢትዮጵያ ለመተግበር ስምምነት ላይ መደረሱንም ጨመረው ጠቁመዋል፡፡ የሁዋዌ ኩባንያ ተወካዮች በበኩላቸው፥ በፈጠራ ላይ የተመሰረቱና ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የተላበሱ ዘላቂ የኢነርጂ መፍትሄ ቴክኖሎጂዎችን በኢትዮጵያ ለመተግበር ቁርጠኛ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ ቴክኖሎጂን አውቆ የሚተገብር ሠራተኛን ለመፍጠር ክህሎት ላይ ያተኮሩ ስልጠናዎችንም እንደሚያመቻቹም ተናግረዋል፡፡ እንዲሁም፥ አገልግሎቱ ለደንበኞቹ የሚሰጠውን አገልግሎት ለማዘመንና የደንበኞችን ቅሬታ ለመቅረፍ ጊዜውን የዋጀ ቴክኖሎጂ ለመተገበር የጀመረው ሪፎርም አካል መሆኑን ለኢዜአ ገልጿል፡፡
ዘመን ገበያ አምራችና ሸማቾችን በቀጥታ በማገናኘት ጥራት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ ለመገበያየት ያስችላል
Dec 19, 2025 151
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 10/2018(ኢዜአ)፦ ዘመን ገበያ አምራችና ሸማቾችን በቀጥታ በማገናኘት ጥራት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ መገበያየት የሚያስችል መሆኑን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሰሀ ይታገሱ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮ ቴሌኮም እና የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በዘመን ገበያ በጋራ መስራት የሚችሉበትን አዲስ አሰራር ይፋ አድርገዋል። ሁለቱ ተቋማት በኢንዱስትሪ ፓርኮች የሚገኙ አምራቾችን ወደ ዘመን ገበያ በማስገባት ለዓለም አቀፍ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ለመጀመሪያ ጊዜ ለሀገር ውስጥ ሸማቾች እንዲያቀርቡ የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት በዛሬው ዕለት ተፈራርመዋል።   ስምምነቱን የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ እና የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍስሃ ይታገሱ (ዶ/ር) ፈርመውታል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሰሀ ይታገሱ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኤሌክትሮኒክ ግብይት በዓለም ዙሪያ ያሉ አምራቾችና ሸማቾችን በማገናኘት ቀልጣፋና ዘመናዊ የግብይት ሥርዓት እየፈጠረ ነው። በኢትዮጵያ የኤሌክትሮኒክ ግብይት ስርዓት በተደራጀ ሳይሆን በተበጣጠሰ መንገድ ሲከናወን እንደነበር አስታውሰው፤ ኢትዮ ቴሌኮም በዘመን ገበያ አማካኝነት ቀልጣፋ የግብይት ስርዓት እየፈጠረ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮም የሀገሪቱን የንግድ ስርዓት በማዘመን አምራቾችና ሸማቾች በቀጥታ በማገናኘት ለንግድ ስርዓቱ መሳለጥ ሚናውን እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ዘመን ገበያ የንግድ ስርዓቱን በማዘመን በኢትዮጵያ መደበኛ የኤሌክትሮኒክ ግብይት መፍጠር ያስችላል ብለዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የተሟላ መሰረተ ልማት በማልማት በሚያስተዳድራቸው 14 የኢንዱስትሪ ፓርኮች ከ200 በላይ ግዙፍ ኩባንያዎች እንዳሉ ገልጸዋል።   በዚህም ዘመን ገበያ አምራቾች ምርታቸውን በቀላሉ ለሸማቹ ማቅረብ እንደሚያስችል ገልጸው፤ ጥራት ያላቸው ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቾች ማቅረብ ያስችላል ብለዋል። ዘመን ገበያ በኢንዱስትሪ ፓርኮች የሚመረቱ የጨርቃ ጨርቅ፣ ምግብ ነክ፣ ኤሌክትሮኒክስ፣ የግንባታ ግብዓትና ሌሎች ምርቶችን የገበያ ጉድለት መሙላት እንደሚያስችል ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያን ከኢንዱስትሪዎች ጥራት ያለው ምርት እንዲያገኙ ያስችላል ያሉት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ የአምራቾችና ሸማቾችን ተጠቃሚነት እንደሚያጠናክር ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮም ቴክኖሎጂዎችን በማዳበር ለኢትዮጵያ ዲጂታል ሽግግር ትልቅ ሚና እየተወጣ መሆኑንም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም