ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የቴክኖሎጂ ክህሎታችችንን በማሳደግ ስራዎቻችንን በላቀ ፍጥነት እንድናከናውን አስችሎናል - ሰልጣኝ ሠራተኞች
Dec 16, 2025 36
ድሬደዋ፣ ታህሳስ 7/2018(ኢዜአ):- የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የቴክኖሎጂ ክህሎታቸውንና ብቃታቸውን በማሳደግ ስራቸውን በላቀ ፍጥነት ለመወጣት እንዳስቻላቸው በድሬደዋ አስተዳደር የተለያዩ ተቋማት ሰልጣኝ ሠራተኞች ተናገሩ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በመላው ሀገሪቷ የተጀመረው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በቴክኖሎጂ በዕውቀትና ክህሎት ተወዳዳሪና ብቁ ባለሙያዎች ለማፍራት መሠረታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። 5 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንን ተጠቃሚ የሚያደርገው ይሄው ሀገርአቀፍ ስልጠና እንደ ሀገር የተጀመረውን ዲጂታል ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ አበርክቶው የላቀ ነው። የዚህ ስልጠና ተጠቃሚ የሆኑ የድሬዳዋ አስተዳደር የመንግስት ሰራተኞች ለኢዜአ እንዳሉት፤ ስልጠናው ሀገራዊ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርምን በተሟላ መንገድ ዳር ለማድረስ የተጀመረውን የዲጂታል አገልግሎት አሰጣጥ ለማቀላጠፍ አስችሏል። ከሰልጣኞቹ መካከል የድሬደዋ አስተዳደር ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ ፍቅሩ ዘውዴ በአራት የተለያዩ ዘርፎች የቀሰሙት የቴክኖሎጂ ክህሎትና ዕውቀት በየትኛውም ዘርፍ ተወዳዳሪና ብቁ ባለሙያ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል። የተቋማቸውን መረጃን በፍጥነትና በላቀ ብቃት በቴክኖሎጂ አውታሮች ለተገልጋዮች ተደራሽ በማድረግ ማህበረሰቡ ከተቋሙ ጋር ትስስሩን እንዲያጠናክር እየሰሩ መሆኑን በመግለፅ ። እንደ አቶ ፍቅሩ ገለፃ ኢትዮ ኮደርስ አገራዊውን የሲቪል ሰርቪሱ ሪፎርም በተሟላ መንገድ ለመተግበር የተጀመረውን ስራ ለማሳካትም የሚያስችል በመሆኑ ሠራተኞች ስልጠናውን በአግባቡ መከታተል ይገባቸዋል። የድሬደዋ አስተዳደር የንግድ፣ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ የዳታ አጠናቃሪ አቶ ከድር ሙስጠፋ እና ስልጠናው የቴክኖሎጂ ክህሎትና ዕውቀታቸውን በማጎልበት በስራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ማስቻሉን ገልጸዋል። ስልጠናው ከስራ ውጭ ባሉ ሰአታት ተደራሽ መደረጉ ደግሞ የመንግሥት ሰራተኛውን ሆነ በየትኛውም ዘርፍ የተሰማራውን ዜጋ ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን በማስታወስ ። የአስተዳደሩ የንግድ፣ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ አሸናፊ አበራ በበኩላቸው ቴክኖሎጂ እንዳይቀድመን እኛ ቀድመን እንድንገኝ አስችሎናል ብለዋል። በነፃ እየተሰጠ የሚገኘው የቴክኖሎጂ ስልጠና የትኛውንም ነዋሪ ተጠቃሚ የሚያደርግና በቴክኖሎጂ ዘርፍ ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋ ለመፍጠር እንደሚያስችል አቶ አሸናፊ አክለው ተናግረዋል ። ስልጠናው ከስራ ሰአታት ውጭ ተደራሽ መደረጉ ደግሞ ከዋናው ስራ በተጓዳኝ የመንግሥት ሰራተኛውን የበለጠ ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን በማስታወስ። በድሬዳዋ አምና 4ሺህ 600 የሚሆኑ ወጣቶችና ሠራተኞች ስልጠናውን በስኬት አጠናቀው የማረጋገጫ ምስክር ወረቀት መቀበላቸው ከድሬደዋ አስተዳደር ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኤጀንሲ የተገኘው መረጃ ያሳያል። ዘንድሮም ከ17ሺህ 600 በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችና ወጣቶች ስልጠናውን ለመከታተል መመዝገባቸውንና ከግማሽ በላይ የሚሆኑት በስልጠና ላይ መሆናቸውም ታውቋል።
ማዕከሉ የገብስ ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል የመነሻ ዘር ብዜት እያከናወነ ነው
Dec 16, 2025 49
ሮቤ፤ታህሳስ 7/2018(ኢዜአ)፦የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል የገብስ ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችል የመነሻ ዘር ብዜት እያከናወነ መሆኑን ገለጸ። ማዕከሉ በተለይ ከዚህ ቀደም በምርምር ከለቀቃቸው ዝርያዎች መካከል 15 የተለያዩ የቆሎና የብቅል ገብስ ዝርያዎች ይገኙበታል። የምርምር ማዕከሉ ስራ አስኪያጅ አቶ ታመነ ሚደቅሳ ለኢዜአ እንዳሉት፥ ማዕከሉ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በምርምር እየደገፈ ነው። በተለይ ማዕከሉ ባለፉት ዓመታት በስንዴ፣ በገብስና በሌሎች ስምንት የትኩረት መስኮች ላይ ምርምሮችን በማካሄድ 116 የምርምር ውጤቶችን ለተጠቃሚው ማድረሱን አስታውሰዋል። ማዕከሉ በአዲስ መልኩ እያከናወናቸው ከሚገኙ የምርምር ተግባራት በተጓዳኝ ከዚህ ቀደም በምርምር ያገኛቸውን የሰብል ዝርያዎች አርሶ አደሩ ዘንድ ተደራሽ ለማድረግ 200 ሄክታር በሚጠጋ መሬት ላይ የመነሻ ዘር ብዜት እያካሄደ መሆኑን በማሳያነት አቅርቧል። በተለይም ባለፉት ዓመታት ባካሄዳቸው ውጤታማ ምርምሮችና በተፈጥሮ ባለው ምቹ ስነ-ምህዳር ብሔራዊ የገብስ ምርምር አስተባባሪ ሆኖ እያገለገለ መሆኑንም አስታውሰዋል። በዚህ ዓመትም የገብስ ምርታማነትን የሚያሳድጉ የመነሻ ዘር ብዜት ስራዎችን በስፋት እያካሄደ መሆኑን ተናግረዋል። የምርምር ማዕከሉ በገብስ ዝርያ ላይ የሚደረጉትን ምርምሮች እያስተባበረ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በማዕከሉ ተመራማሪና የብሔራዊ የገብስ ምርምር አስተባባሪ ወይዘሮ ህይወት ሰብስቤ ናቸው። የሲናና ግብርና በተለይ ባለፉት ዓመታት በገብስ ላይ ባካሄደው ውጤታማ ምርምር ዘጠኝ የምግብ ገብስ፣ ሁለት የቆሎና አራት የብቅል ዝርያ ገብስ ለተጠቃሚዎች ማድረሱን አመልክተዋል። በማዕከሉ ከተለቀቁት የምግብ ገብስ መካከል በአንድ ሄክታር እስከ 65 ኩንታል ምርት የሚሰጡ ''ወለሼ''ና ''ጌሴ'' የሚል ስያሜ የተሰጣቸው እንደሚገኙበት አስታውሰዋል። እንዲሁም የብቅል ፋብሪካ ፍላጎትን የሚያሟሉና በአንድ ሄክታር ከ50 ኩንታል በላይ ምርት የሚሰጡ ''ሲንግተን''ና ''ሞአታ'' የሚል ሲያሜ ያገኙ የብቅል ገብሶችንም ጠቅሰዋል። ወይዘሮ ህይወት እንዳሉት፣ ሲናናን ጨምሮ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ የምርምር ማዕከላት ባለፉት ዓመታት በገብስ ዝርያ ላይ ባከናወኗቸው ምርምሮች ለምግብ ፍጆታነት ከማዋል ባሻገር ከውጭ ይገባ የነበረውን የብቅል ገብስ በሀገር ውስጥ ምርት በመተካት የውጭ ምንዛሪ በማዳን ረገድ ጉልህ ድርሻ እያበረከቱ መሆኑን አመልክተዋል።
ፋይዳ መታወቂያ የሴቶችን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ወሳኝ ጉዳይ ነው
Dec 16, 2025 60
አዲስ አበባ፤ታኅሣስ 7/2018(ኢዜአ)፡-ፋይዳ የዲጂታል መታወቂያ የሴቶችን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትልቅ ሚና እንዳለው የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሂክማ ከይረዲን ገለፁ። የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የፋይዳ ዲጅታል መታወቂያ ምዝገባ የሴቶች ንቅናቄና የግንዛቤ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሂክማ ከይረዲን እንዳሉት፥ የፋይዳ የዲጂታል መታወቂያ የሴቶችን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትልቅ አቅም ይፈጥራል። ፋይዳ ለሴቶች፣ ህፃናትና አካል ጉዳተኞች የእኩልነት መብት ማረጋገጫና የማስፈፀሚያ መሳሪያ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ሴቶችን ጨምሮ ሁሉም ህብረተሰብ የፋይዳ መታወቂያ ምዝገባ ማድረግ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና ዳይሬክተር ዮዳሄ አርዓያ ሥላሴ በበኩላቸው፥ መንግስት ዜጎችን ሙሉ ለሙሉ የዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ ለማድረግ እየሰራ እንደሆነ ጠቅሰዋል። ዲጂታል መታወቂያ ዲጂታል ኢኮኖሚ በመገንባት የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ ያለመ መሆኑን በኢትዮጵያ ነዋሪ የሆነ ማንኛውም ሰው ራሱን የሚገልጽበትና መብቱን የሚያረጋግጥበት መለያ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በርካታ ዜጎች የዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ማድረጋቸውን ጠቅሰው፥ በቀጣይ ወደ ዞንና ወረዳ ድረስ በመውረድ የመመዝገብ ስራዎች እንደሚከናወኑ ተናግረዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የፋይዳ መታወቂያ ምዝገባን ለማሳካት የሴቶች ተሳትፎ ቁልፍ ሚና እንዳለውም ገልጸዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ እስካሁን ለፋይዳ መታወቂያ ከተመዘገቡ ዜጎች መካከል 40 በመቶዎቹ ሴቶች መሆናቸው ታውቋል።
የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ክህሎታችንን አሳድጎታል-ሰልጣኞች
Dec 16, 2025 45
አሶሳ፤ታህሳስ 7/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ክህሎታቸውን በማሻሻል ተወዳዳሪነታቸውን እንዳሳደገው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሰልጣኞች ተናገሩ። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተነደፈው የ5 ሚሊዮን ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከተቀመጡት የ100 ፐርሰንት ግቦች አንዱ ነው። ይህም የዜጎችን የዲጂታል ክህሎት በማሳደግ ብቁና ተወዳዳሪ እንዳደረጋቸው ስልጠናውን የወሰዱ ዜጎች ይገልጻሉ። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ከተማ ስልጠናውን ከወሰዱ ሰዎች መካከል የሻምበል በዛብህ እንደገለፀው፥የ5 ሚሊየን ኮደርስ ኢንሼቲቭ የዜጎችን የዲጂታል ዕውቀት በማሳደግ ወቅቱ የሚፈልገውን የሰለጠነ የሰው ሀይል ለመፍጠር ያግዛል። ስልጠናው ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ከሚኖረው ፋይዳ በተጨማሪ ዜጎች የዲጂታል ዕውቀታቸውን በማዳበር አዳዲስ የቴክኖሎጂ መተግበሪያዎችን ለማልማት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ከኢትዮ-ኮደርስ ኢንሼቲቭ ኮርሶች አራቱን ያጠናቀቀው ሌላው ሰልጣኝ ብርሃኑ ሽታነህ እንዳለው፥ የኢትዮ -ኮደርስ ኢንሼቲቭ ዜጎች ራሳቸውን ለማብቃት መልካም አጋጣሚ መሆኑን ብለዋል። ስልጠናው መደበኛ ስራውን ለማሳደግና በትርፍ ጊዜው የጀመረውን ስራ ውጤታማ ለማድረግ አቅም እንደፈጠረለት ተናግሯል። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በሶስት ዓመት ውስጥ 65 ሺህ ዜጎች ስልጠናውን እንዲወስዱ ዕቅድ ተይዞ ወደ ተግባር መገባቱን የገለፁት ደግሞ የክልሉ ሳይንስ፤ ቴክኖሎጂና ኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ይታያል በላይ ናቸው። በክልሉ እስካሁን ድረስ ከ12 ሺህ 200 በላይ ዜጎች ስልጠናውን እየተከታተሉ መሆኑን የገለፁት ዋና ዳይሬክተሩ፥ በክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ ነው ብለዋል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሻሻል የዜጎችን አቅም ከማሳደግ ባለፈ ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት ለተያዘው ዕቅድ ወሳኝ በመሆኑ የዜጎችን ተሳትፎ እንደሚጠይቅ ገልጸዋል። በክልሉ የኮደርስ ስልጠናን በተቀናጀ ሁኔታ ለማስኬድ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመተባበር ዜጎች ስልጠናውን እንዲወስዱ እየተደረገ መሆኑን ዋና ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል።
ዩኒቨርሲቲው አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ነው
Dec 16, 2025 51
አርባምንጭ፤ ታህሳስ 7/2018 (ኢዜአ) ፡-የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን ገለጸ። አርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማርና ከምርምር ሥራ በተጓዳኝ በማህበረሰብ አገልግሎት ስራው አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ ነው፡፡ በዩኒቨርሲቲው የምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዚዳንት ተክሉ ወጋየሁ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በዕውቀት ላይ የተመሰረተ የማህበረሰብ አገልግሎት ላይ መስራት ይገባቸዋል። የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲም አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ ሲሆን በዚህም በጋሞ፣ በጎፋ፣ በባስኬቶ፣ በኮንሶ፣ በጋርዱላና በአሌ ዞኖች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ስራዎች ተሰርቷል ብለዋል፡፡ በጋሞ ዞን ካምባ ዙሪያ ወረዳ ድንጋሞ ቀበሌ ከ400 በላይ ነዋሪዎችን የሃይል ተጠቃሚ ያደረገ 15 ኪሎ ዋት የሚያመነጭ ታዳሽ ሃይል ፕሮጀክት ገንብቶ በቅርቡ ለአገልግሎት ማብቃቱን ለአብነት ጠቅሰዋል። በገጠር የሚገኙ ማህበራዊ ተቋማትን የሃይል ተጠቃሚ ለማድረግ በተከናወነ ተግባርም በአጎራባች ዞኖች የሚገኙ 24 ጤና ጣቢያዎችና 19 ትምህርት ቤቶችን የሶላር ሃይል አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የእንሰት መፋቂያና ማብላያ ቴክኖሎጂዎችን በመፍጠርና በማላመድም በአምራች አርሶ አደሮች ላይ ይደርስ የነበረውን የጊዜና ጉልበት ብክነት በመቀነስ የቆጮ ማብላያ ሂደትን ማሳጠር ማስቻሉን ገልጸዋል። በቴክኖሎጂው በመታገዝ ከእንሰት ምርት ኩኪስና ሌሎች ምግቦችን መስራት መቻሉን ጠቅሰው፤ ቴክኖሎጂው ለብዙዎች የሥራ ዕድል የሚፈጥር በመሆኑም እንሰት አምራች በሆኑ በሲዳማና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች የማስፋት ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል፡፡ ሙዝን ወደ ዱቄት የሚቀይር ቴክኖሎጂ በመፍጠርም ዜጎች የተለያዩ ምግቦችን በማዘጋጀት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያስችል ስራ መከናወኑንም ገልጸዋል፡፡ በጋሞና ወላይታ ዞኖች በሚገኙ ሶስት ወረዳዎች በ100 ሄክታር መሬት ላይ ሃሌኮ ወይም ሽፈራው ቅጠልን ሜካናይዝድ በሆነ መንገድ የማልማት ስራን ጨምሮ በምርምር የታገዘው የተጎዳ አፈርን ለማከም የሚያስችል የተፈጥሮ ማዳበሪያ ውጤታማ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በዞኑ ሥር የሚገኙ የገዜ ጎፋ፣ የመሎ ጋዳ እና መሎ ኮዛ ወረዳ ማህበረሰብን ተጠቃሚ ያደረጉ በርካታ ተግባራት ማከናወኑን ገልጸዋል። በተለይም የጤና አገልግሎቱን ጥራትና ተደራሽነት ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት እያገዘ መሆኑን ጠቅሰው የመሎ ጋዳ ወረዳ ጤና ጣቢያን የሶላር ተጠቃሚ ማድረጉን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው አጠገባችን የሚገኘውን የድንጋሞ ወንዝ ተጠቅሞ የሃይል ተጠቃሚ አድርጎናል ያሉት ደግሞ በጋሞ ዞን ካምባ ዙሪያ ወረዳ የድንጋሞ ቀበሌ አስተዳደር አቶ ከድር ካማ ናቸው።
የዲጂታል ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ቁልፍ መሠረተ-ልማቶችን የመጠበቅ ሥራ እየተከናወነ ነው
Dec 16, 2025 83
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 7/2018 (ኢዜአ)፡- የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር በዋናነት የዲጂታል ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ቁልፍ መሠረተ-ልማቶችን ከጥቃት መከላከል የሚያስችሉ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገለጸ። በኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር የሳይበር መከላከል ዳይሬክተር መሀመድ ፈረጃ፤ የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል በተለይ ቁልፍ መሠረተ-ልማት ላይ የሚከናወኑ የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል ሀገራችን የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደርን ዐዋቅራ እየሠራች ነው ብለዋል። በተጨማሪም በዲጂታል 2025 ላይ የጸደቀው ስትራቴጂ የሳይበር ደኅንነትን እንደ አንድ ምሰሶ ወስዶ በከፍተኛ ሁኔታ እንዲሠራበት እና ተቋማት የየራሳቸውን ኢኒሼቲቭ ቀርጸው ራሳቸውን እንዲከላከሉ ጭምር እያስቻለ መሆኑን አመላክተዋል። በ2024 የጸደቀው የግል መረጃዎች ጥበቃ ዐዋጅ የቁልፍ መሠረተ-ልማቶች ባለቤቶች ለሳይበር ጥቃት እንዳይጋለጡ በመጠበቅ ከፍተኛ እገዛ እያበረከተ መሆኑንም ተናግረዋል። በኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር የተዘጋጀ የቁልፍ መሠረተ-ልማቶች ጥበቃ ረቂቅ ዐዋጅ መኖሩንም ጠቁመው፤ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቀርቦ በዚህ ዓመት እንደሚጸድቅ ይጠበቃል ብለዋል። ይህም ቁልፍ መሠረተ-ልማቶችን ለመጠበቅ ከፍተኛ ዐቅም እንደሚሆን ነው ለኢዜአ የተናገሩት። በተጨማሪም በሴክተሮች ላይ ምን ዓይነት አዳዲስ ስጋት አለ? የሚለውን በመከታተል በሴክተሮቹ ላይ የሚያጋጥመውን ስጋት ከሴክተሩ ባለቤት ጋር በመሆን የመቀነስ ሥራ እንደሚከናወን ጠቁመዋል። በዘርፉ ያለውን የክኅሎት ክፍተት ለመሙላት ተቋሙ ከትልልቅ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር ጥምረት በመፍጠር በሁለተኛ እና ሦስተኛ ዲግሪ ደረጃ የሳይበር ደኅንነት ትምህርት እየተሰጠ እንደሚገኝም አንስተዋል።
የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ለግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ቁልፍ ጉዳይ ነው- ሚኒስትር አዲሱ አረጋ
Dec 15, 2025 147
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 6/2018(ኢዜአ)፦የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ለግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ቁልፍ ጉዳይ በመሆኑ አርሶና አርብቶ አደሮች እንዲመዘገቡ በቅንጅት መሥራት እንደሚገባ የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ። በሚቀጥሉት 3 ወራት 12 ሚሊየን አርሶና አርብቶ አደሮች ለፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ እንዲመዘገቡ ግብ መያዙንም ጠቅሰዋል። ግብርና ሚኒስቴር ከብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራምና ከክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊዎች ጋር በመሆን ዲጂታል መታወቂያን በገጠር ለማስፋት እና ዜጎችን ከተረጂነት ወደ አምራችነት ለማሸጋገር በተያዙ ግቦች ላይ ውይይት አካሂደዋል። የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ እንዳሉት የግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ስኬታማ ለማድረግ ዲጂታል መታወቂያን ለሁሉም ተደራሽ ማድረግ አስፈላጊ ነው። አርሶ እና አርብቶ አደሩ ዘርፈ ብዙ ተጠቃሚ የሚያደርገውን የዲጂታል መታወቂያ በመመዝገብ እንዲይዝ ለማድረግ የተቀናጀ ስራ መስራት ይገባል ነው ያሉት። ፋይዳ መታወቂያ የግብርና ትራንስፎርሜሽንን፣ የገጠር ፋይናንስን የአርሶ አደሮች መረጃ አያያዝን፣ የመሬት አስተዳደር ስርዓትን ለማዘመን ቁልፍ ጉዳይ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በመሆኑም በሚቀጥሉት ሦስት ወራት ከ12 ሚሊየን በላይ የገጠር ነዋሪዎች የብሔራዊ መታወቂያ እንዲመዘገቡ የተያዘውን እቅድ ለማሳካት የሁሉም ርብርብ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ተረጅነትን ዜሮ በማድረስ ግብ መሰረት ከአራት ሚሊዮን በላይ የገጠር ልማታዊ ሴፍቲኔት ተጠቃሚዎችን እስከ ታህሳስ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ከተረጅነት ለማላቀቅ ግብ መቀመጡን ጠቁመዋል። በመሆኑም ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር የተያዘው ዕቅድ እንዲሳካ ክልሎች የተቀናጀ ስራን ማጠናከር እንደሚገባቸው ተናግረዋል። የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና ዳይሬክተር ዮዳሄ አርዓያሥላሴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት እስከ ሰኔ 30/2018 ዓ.ም ድረስ የፋይዳ መታወቂያ ተመዝጋቢዎችን 90 ሚሊየን ለማድረስ ታቅዶ እየተሰራ ነው። ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳለው ገልጸው በሚቀጥሉት ሦስት ወራት ለታቀደው ግብ መሳካት የባለድርሻ አካላት ትብብር ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል። የፋይናንስ ተደራሽነት፣ የግብርና ግብዓት፣ የአገልግሎት ተደራሽነትን፣ ለማፋጠን ዲጂታል መታወቂያ ትልቅ አስተዋዕጾ እንዳለው ገልጸዋል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ጌቱ ገመቹ በበኩላቸው በክልሉ የገጠር ነዋሪዎችን የዲጂታል መታወቂያ እንዲመዘገቡ ለማድረግ የተያዘውን ግብ ከታቀደው በላይ ለመፈጸም በቁርጠኝነት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በክልሉ በሴፍቲኔት ተጠቃሚ የሆኑ ዜጎችን ከተረጂነት ለማላቀቅ የሚያስችሉ ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውንም ነው ያነሱት። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) በበኩላቸው አርሶና አርብቶ አደሩን ከተረጂነት ለማላቀቅ እና አምራችነትን ለማበረታታት የተጀመሩ ስራዎች በክልሉ በጥሩ ሁኔታ ላይ ናቸው ብለዋል። ዘመናዊ አርሶ አደር ለመፍጠር ወሳኝ የሆነውን የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ለማሳካት እንደሚሰራ ጠቁመዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪ እና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ዑስማን ሱሩር በበኩላቸው ከተረጂነት ለመላቀቅ የተሰሩ ስራዎች ስኬታማ ናቸው። ዲጂታል መታወቂያን በተመለከተ ግንዛቤን በማጠናከር አርሶና አርብቶ አደሩ በስፋት እንዲመዘገብ እንተጋለን ብለዋል።
በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል እና አገልግሎቶቹን የማስፋት ሥራ እየተከናወነ ነው
Dec 14, 2025 123
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 5/2018(ኢዜአ)፡- መሶብ የአንድ ማዕከልንና የሚሰጡ የአገልግሎት ዓይነቶችን ለማስፋት እየተሠራ መሆኑን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሠመረ ጂራታ(ኢ/ር) ተናገሩ። ለዜጎች የሚሰጥ አገልግሎት ከቅሬታ የጸዳ፣ ጊዜና ወጭ ቆጣቢ፣ ፍትሐዊ ብሎም ተደራሽ እንዲሆን ማስቻል የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ዓላማ መሆኑን አስገንዝበዋል። እንደ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከመስከረም 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአምሥት የክልል እና በሦስት የፌደራል ተቋማት በ33 ዘርፎች አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። እስካሁንም ከ6ሺህ 300 በላይ ተገልጋዮች አገልግሎት ማግኘታቸውን አስታውቀዋል። በቀጣይ ወደ ማዕከሉ የሚገቡ ተቋማትና አገልግሎቶችን ቁጥር የማስፋት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። በዚህም መሠረት ተጨማሪ አንድ የፌደራል እና ሦስት የክልል ተቋማት ወደ መሶብ የአንድ ማዕከል መግባት የሚያስችላቸውን ሥራ እያከናወኑ ነው ብለዋል። ይህን ተከትሎም በአጭር ጊዜ አምሥት ተጨማሪ አገልግሎቶች ወደ ማዕከሉ እንደሚገቡ አመላክተዋል። በሌላ በኩል በአሶሳ ከተማ አሥተዳደር ደረጃ መሶብ የአንድ ማዕከል እንዲኖር እየተሠራ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
በክልሉ የኮደርስ ስልጠና መርሐ ግብር በተጠናከረ መልኩ እየተከናወነ ነው
Dec 13, 2025 182
ሚዛን አማን ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ):- የኮደርስ ስልጠና መርሃ ግብር በተጠናከረና በተቀናጀ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ አስታወቀ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለ5 ሚሊዮን ዜጎች ነፃ የኮደርስ የስልጠና እድል በመመቻቸቱ እስካሁን በርካቶች የእድሉ ተጠቃሚ ሆነዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ምትኩ አስፋው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ 138 ሺህ ዜጎችን ለማሰልጠን ዕቅድ የተያዘ ሲሆን ከእነዚህም መካከል እስካሁን 16 ሺህ 700 የሚሆኑት ስልጠናውን አጠናቀው የምሥክር ወረቀት አግኝተዋል። በተያዘው ዓመትም የስልጠናው ሂደት ተጠናክሮ የቀጠለ በመሆኑ ተጨማሪ 63 ሺህ ዜጎችን የማሰልጠን እቅድ ተይዞ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የስልጠናው ዓላማ በዘርፉ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሆኑ ዜጎችን ማፍራት መሆኑን የተናገሩት ኃላፊው የእድሉ ተጠቃሚ ለመሆን ጊዜ ሳያባክኑ መመዝገብና መሰልጠን ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። ሥልጠናውን ወስደው ሰርተፊኬት ከተቀበሉት መካከል የሲዝ ከተማ አስተዳደር ነዋሪው ወጣት ምናሉ ግዛቸው፤ በሥልጠናው ከዘመኑ ጋር ተወዳዳሪ እንድሆን የሚያስችለኝን እውቀት አግኝቻለሁ ብሏል። በወሰዳቸው አራት ኮርሶች ከመሠረታዊ የኮምፒዩተር እውቀት ጀምሮ አርተፊሻል ኢንተለጀንስ እና ፕሮግራሚንግ ላይ በቂ ክህሎት ማግኘቱን ተናግሯል። የሥልጠና አሰጣጥ ሁኔታው ቀላልና ለመያዝ ምቹ በመሆኑ ማንኛውም ሰው ጊዜ ብቻ ሰጥቶ ዕድሉን መጠቀም እንዳለበት ነው የተናገረው።
ሰልጣኞች በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዲጂታል ቴክኖሎጂ ዕውቀታቸው ዳብሯል
Dec 13, 2025 202
አርባምንጭ ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ):- የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የቴክኖሎጂ ዕውቀታቸውን እንዳዳበረው የአርባምንጭ ከተማ ሠልጣኞች ገለጹ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የአርባ ምንጭ ከተማ የኢትዮ-ኮደርስ ሰልጣኞች መካከል ወጣት ሊዲያ ዳሾ፤በአንድሮይድ ደቨሎፕመንት፣ ዳታ አናሊስስ፣ አርተፊሻል ኢንተለጀንስና ፕሮግራሚንግ ዘርፎች ስልጠና በመከታተል በአለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርጋትን የምስክር ወረቀት መውሰዷን ገልጻለች። ወቅቱ የሚጠይቀውን የሰው ሠራሽ አስተውሎት ዕውቀት መያዝ አስገዳጅ በመሆኑ ለዚሁ ራሷን ማብቃቷን አስረድታለች። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የኦን ላይን ሥራዎችን ለመወዳደርና የሥራ ዕድሎችን ለመፍጠር ምቹ ሁኔታ ያለው መሆኑንም ተናግራለች፡፡ ሌላኛው ሠልጣኝ ወጣት ኦሳ ፋንታ በበኩሉ፤ በፕሮግራሚንግ እና ኮዲንግ ዘርፎች ስልጠና በመውሰድ የምስክር ወረቀት አግኝቷል። ስልጠናው ወቅቱን የዋጀ የቴክኖሎጂ ክህሎት በማላበስ አለም አቀፍ ተወዳዳሪነቱን እንደሚጨምርለት ተናግሯል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መንግስት ወጪውን መሸፈኑ ዜጎችን ለማብቃትና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለማድረግ የታለመ ትልቅ ዕድል ነው ብሏል። የምስክር ወረቀቱ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ያለው መሆኑ በየትኛውም ሀገር የሥራ እድልን ለማግኘት መሰረት እንደሚጥል ገልጿል። የአርባምንጭ ከተማ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ሃላፊ አቶ በሃይሉ ካፒቴን ፤ መንግስት የዜጎችን የቴክኖሎጂ ዕውቀት ለማሳደግ የጀመረው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በርካታ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረጉን ተናግረዋል። በተለይ ለወጣቶች ዕውቀታቸውን በማሳደግ ለስራ ፈጠራ በማዋል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንዲያሳድጉ የሚረዳ ነው ብለዋል፡፡ የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና እንደ ሀገር ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በአርባምንጭ ከተማ 4 ሺህ 455 ዜጎች ስልጠና ወስደው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም 4 ሺህ ዜጎችን ለማሠልጠን ግብ ተይዞ እየተሰራ ሲሆን በእስካሁኑ 2 ሺህ 829 ዜጎች መሠልጠናቸውን ገልጸዋል።
አዲሱ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግር አቅም ይሆናል
Dec 13, 2025 153
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ አዲሱ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግር አቅም እንደሚሆን የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴዔታ ተሻለ በሬቻ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠንካራ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ተቋማትን በመገንባት በእውቀትና ክህሎት የበቃ የሰው ኃይል ማፍራት የሚያስችል አዲስ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ ተዘጋጅቶ ስራ ላይ መዋሉ ይታወቃል። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴዔታ ተሻለ በሬቻ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ አዲሱ ስትራቴጂ የአረንጓዴ የክህሎት ልማት የስልጠና ፕሮግራሞችን የያዘ እና ለታዳሽ ኃይል ትኩረት የሰጠ ነው። ወደ አረንጓዴ ኢኮኖሚ በሚደረገው ሽግግር ብቃትና ክህሎት ያለው የሰው ኃይል ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ስትራቴጂው ብቃት ያለው እና ለአካባቢ ተስማሚ ቴክኖሎጂዎችን የሚተገብርና ሃብትን በቁጠባ የሚጠቀም ትውልድ ለመገንባት እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡ ሥርዓተ-ትምህርቶችን በአረንጓዴ የስራ መርሆዎችና አሠራሮች በማበልጸግ ተማሪዎች ከተቋማት ሲወጡ ለአካባቢ ተስማሚ የሆኑ ዘዴዎችንና መሣሪያዎችን እንዲጠቀሙ ያስችላል ብለዋል፡፡ አዲሱ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግር አቅም እንደሚሆንም ነው ሚኒስትር ዴዔታው የተናገሩት፡፡ በአዲሱ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና ስትራቴጂ መሰረት የአረንጓዴ ቴክኒክና ሙያ ልጠና ፓኬጅ ተቀርጾ ወደ ስራ መግባቱን አመላክተዋል፡፡፡ ይህ ፓኬጅ ከብክለትና ከብክነት የጸዳ የሃይል አጠቃቀም እንዲኖር ያስችላል ብለዋል፡፡ በተቋማት ውስጥ ዘመናዊ እና ለአካባቢ ተስማሚ የሆኑ የማሰልጠኛ መሣሪያዎችን በማስገባት ተማሪዎች በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እንደሚሰራም ተናግረዋል፡፡ ተማሪዎች በንድፈ ሃሳብ ብቻ ሳይሆን በዘመናዊ አረንጓዴ ቴክኖሎጂዎች ተግባራዊ ልምምድ በማድረግ በሥራ ዓለም ውስጥ የአረንጓዴ ልምዶችን የመተግበር ብቃት እንዲኖራቸው እየተደረገ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ከዓለም አቀፍ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ መስፋፋት ጋር ተያይዞ የሚፈጠሩ አዳዲስ የስራ ዕድሎችን መጠቀም እንደሚያስችልም እንዲሁ፡፡
በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሰጣጥ ቀልጣፋ አገልግሎት እያገኘን ነው - ተገልጋዮች
Dec 13, 2025 114
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 4/2018(ኢዜአ)፡- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እያገኘነው ያለው አገልግሎት ፈጣን እና እንግልትን የቀረፈ ነው ሲሉ ተገልጋዮች ገለጹ። በማዕከሉ አገልግሎት አግኝተው ሲመለሱ ኢዜአ ያነጋገራቸው ተገልጋዮች እንዳሉት፤ ነባሩ አገልግሎት አሰጣጥ ከአንዱ ወደ ሌላው ተቋም መመላለሱ ብሎም ቶሎ ጉዳይን ለመፈጸም አድካሚና የቅሬታ ምንጭ ነበር። አቶ ሙፍቲ መርቀኒ ለዓመታት አገልግሎት ለማግኘት ወደ ተቋማት ይመላለሱ እንደነበር አውስተው፤ ያኔ አገልግሎት አሰጣጡ ረጅም ጊዜ የሚወስድና ጉዳያቸውም ውሎ ያድር እንደነበር አስታውሰዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሥራ ከጀመረ ወዲህ አራት ጊዜ ለአገልገሎት መምጣታቸውንና በርካታ ተቋማት በአንድ ቦታ በመኖራቸው ጉዳያቸውን በቀላሉ መፈጸም መቻላቸውን ተናግረዋል። የንግድ ፈቃድ ለማውጣት ወደ ማዕከሉ መምጣታቸውን ጠቁመው፤ ከጠበቁት በተሻለ ፍጥነት በመስተናገዳቸው በአገልግሎቱ መርካታቸውን አስታውቀዋል። አክሲዮን ለማሻሻል፣ የንግድ ምዝገባ ለማከናወንና የንግድ መለያ ቁጥር ለማውጣት ወደ ማዕከሉ ያቀኑት ዝነኛው መዝገቡ በበኩላቸው፤ በ20 ደቂቃ ውስጥ ቀልጣፋ አገልግሎት በማግኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። ዛሬን ጨምሮ በማዕከሉ ሁለት ጊዜ አገልግሎት ለማግኘት በማዕከሉ መገኘታቸውን ጠቁመው፤ አገልግሎት አሰጣጡ ምቹ እና ድካምን ያስቀረ ነው ብለዋል። ጽጌ ዳኛው በበኩላቸው ማኅበር ለማጸደቅና ስያሜ ለማውጣት ወደ ማዕከሉ መምጣታቸውን ጠቅሰው፤ በአምሥት ደቂቃ ውስጥ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ማዕከሉ ከመጀመሩ በፊት ግን የሲስተም ችግር፣ የተቋማት በተለያየ ቦታ መሆንና የወረፋ መብዛትን ተከትሎ መስተጓጎል ያጋጥም እንደነበር አውስተዋል። ለተለያዩ አገልግሎቶች በተደጋጋሚ ወደ ማዕከሉ መምጣታቸውን አንስተው፤ ከበር ጀምሮ እስከ መጨረሻ አገልግሎት አሰጣጥ ድረስ ጥሩ አገልግሎት እየተሰጠ እንደሚገኝ መስክረዋል። ከጠበቅነው ጊዜ በተሻለ ፍጥነት ተስተናግደናል ያሉት ተገልጋዮቹ፤ ወጪና ጊዜን በመቆጠብ ብሎም ከአንድ ወደ ሌላ ተቋም በመመላለስ የሚከሰት እንግልትን በማስቀረት በአጭር ጊዜ አገልግሎት አግኝተናል ብለዋል።
ዓለም አቀፍ ሁኔታን ያገናዘበ የጤና ስርዓት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ሰው ሰራሽ አስተውሎት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
Dec 12, 2025 123
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፍ ሁኔታን ያገናዘበ የጤና ስርዓት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ሰው ሰራሽ አስተውሎት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሒ ገለፁ። ጤና ሚኒስቴር "የሰው ሰራሽ አስተውሎትና የቴሌ ጤና ቴክኖሎጂ ለጤናው ዘርፍ የሚኖራቸው የወደፊት ሚና" በሚል መሪ ሀሳብ የባለድርሻ አካላት ውይይት አካሒዷል። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሒ እንደገለፁት መንግስት የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል። የጤና አገልግሎትን ከሰው ሰራሽ አስተውሎትና ቴሌ-ጤና ቴክኖሎጂ ጋር በማቀናጀት ተደራሽ እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። ለህክምና አገልግሎት የሚሰበሰቡ መረጃዎች ላይ በመመስረት የሚሰጡ አገልግሎቶችን ለማጠናከር የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን መጠቀም ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። በተለይም በወረርሽኝና በተፈጥሮ አደጋዎች ቅድመ ትንበያና የተቀናጀ ምላሽ አሰጣጥ ላይ አይነተኛ ሚና እንዳለውም ጠቁመዋል። የጤና ስርዓቱን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር አዳዲስና ፈጠራ የታከለባቸው ቴክኖሎጂዎች በተገቢው መልኩ ተግባራዊ እየተደረጉ መሆኑንም አንስተዋል። በ2016 ዓ.ም የተሻሻለው አዲሱ የጤና ፖሊሲ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ በተገቢው መልኩ ጥቅም ላይ መዋሉን የሚደግፍ መሆኑ ለአተገባበሩ አስቻይ ሁኔታ መፍጠሩን ነው የጠቀሱት። በተለይም ለጤና ምርመራ፣ በታካሚዎች መረጃና የህክምና ታሪክ ላይ የተመሠረተ አገልግሎት ለመስጠትና በርቀት ለሚሰሩ የቴሌ ጤና አገልግሎት መጠናከር ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። ዓለም አቀፍ ሁኔታን ያገናዘበ የጤና ስርዓት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን ሀላፊነት እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። በጤና ሚኒስቴር የጤና ስርዓት ኢኖቬሽንና ጥራት መሪ ስራ አስፈጻሚ ዶክተር አባስ ሃሰን በበኩላቸው፤ የጤና አገልግሎት ጥራትን በማረጋገጥ ሒደት ባለድርሻ አካላት ያላቸው ሚና የጎላ መሆኑን ገልጸዋል። የጤናውን ዘርፍ ከሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ ጋር አጣጥሞ ተግባራዊ ለማድረግ ለተጀመረው ጥረት በዘርፉ የሚሰሩ ባለድርሻ አካላት የሚጠበቅባቸውን ድጋፍ እያደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል። በኢትዮ-ቴሌኮም የኢንተርፕራይዝ ሶሉዩሽን ቺፍ ኦማድረግ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የጤና ስርዓቱን የሚያዘምኑ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች በጤና ተቋማት ተግባራዊ መደረግ መጀመራቸውን ነው የጠቀሱት። የጤና ተቋማትን በአንድ ቋት በማስተሳሰር መረጃን በቀላሉ ማግኘት የሚያስችለው ቴክኖሎጂ በጋራ ትብብር መልማቱን አንስተዋል።
አገልግሎቱ አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረጉ ቀልጣፋና አስተማማኝ አገልግሎት እንድናገኝ አስችሎናል
Dec 12, 2025 113
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረጉ ቀልጣፋና አስተማማኝ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ተገልጋዮች ገለጹ። የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቶፊክ ሻፊ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት አገልግሎቱ አሰራሩን ዲጂታላይዝ በማድረጉ ደንበኞች ቀልጣፋና አስተማማኝ መስተንግዶ እያገኙ ነው። አገልግሎቱ ሀሰተኛ ሰነዶችን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር የቴክኖሎጂ ትስስር መፍጠር በመቻሉና የፋይዳ መታወቂያን በአስገዳጅነት በመጠቀሙ ችግሩን በመከላከል ረገድ ውጤታማ ስራ ማከናወኑን ገልጸዋል። የመረጃ ቋት ስርዓት በመዘርጋት ሀገራዊ ሰነድ የማረጋገጥና የመመዝገብ ስራ እየተከናወነ መሆኑንም አስታውቀዋል። የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓትን በማጠናከርና ተደራሽነትን በማስፋት ተገልጋዮች ያለ ወረፋ እንዲስተናገዱ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም ተናግረዋል። በዚህም አገልግሎቱ ባሉት ቅርንጫፎች ለተገልጋዮች ፍላጎት ፈጣን ምላሽ በመስጠት ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። ተቋሙ በአጠቃላይ ከወረቀት ወደ ዲጂታላይዜሽን የሚያደርገው ሽግግር በተሳካ ሁኔታ እየሄደ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። የንግድና ኢንቨስትመንት ስራዎች እንዲሳለጡና የማህበራዊ መስተጋብር ጤናማነት እንዲረጋገጥ አገልግሎቱ የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ ተገልጋዮች በበኩላቸው በተቋሙ ባገኙት አገልገሎት ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል አቶ ከበደ ወልደጊዮርጊስ እንዳሉት ተቋሙ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ እየሰጠ ባለው ቀልጣፋ አገልግሎት በመታገዝ በአጭር ጊዜ ጉዳያቸውን አጠናቀው መመለስ ችለዋል። በተቋሙ እየተሰጠ ያለው አገልግሎት ከዚህ በፊት ከነበረው አንጻር መሻሻሉንም ነው የተናገሩት። ወይዘሮ ዘሃራ መሀመድ በበኩላቸው ባገኙት አገልግሎት መደሰታቸውን ገልጸው የሚሰጠው አገልግሎት ከነበረው በእጅጉ መሻሻሉን ገልጸዋል። በዚህም በምቹ የአገልግሎት መስጫ ቦታ በአጠረ ጊዜ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘታቸውን ነው የጠቆሙት። የተቋሙ የአገልግሎት አሰጣጥ በቴክኖሎጂ የታገዘ እና ቀልጣፋ በመሆኑ ጥሩ አገልግሎት ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ አቶ አንዋር አህመድ ናቸው። ቀደም ሲል ከወረፋ ጋር በተያያዘ ይታዩ የነበሩ ችግሮች አሁን ላይ መቀረፋቸውን ተናግረዋል።
የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎትን በማዘመን ህብረተሰቡ ፈጣንና ወጪ ቆጣቢ አገልግሎት እንዲያገኝ እየተደረገ ነው
Dec 12, 2025 103
አሶሳ፤ ታህሳስ 3/2018 (ኢዜአ)፦ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎትን በማዘመን ህብረተሰቡ ፈጣንና ወጪ ቆጣቢ አገልግሎት እንዲያገኝ እየተደረገ መሆኑን የፌዴራል የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሀሚድ ኪኒሶ ተናገሩ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፍትህ ቢሮ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባን በዲጂታል የታገዘ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል። በዕለቱ የተገኙት የፌደራል የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሀሚድ ኪኒሶ እንደተናገሩት፤ ዜጎች በሁሉም ዘርፍ በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት እንዲያገኙ በማድረግ ብልሹ አሰራርን ለማስቀረት እየተሰራ ነው። የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት በርካታ ተገልጋዮችን የሚያስተናግድ በመሆኑ በሀገር አቀፍ ደረጃ አገልግሎት አሰጣጡን የማዘመን ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ሀረሪ፣ ሲዳማና አማራ ክልሎች ዲጂታል የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት እያከናወኑ መሆኑን የተናገሩት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፍትህ ቢሮም በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ስራ መግባቱን ጠቁመዋል። አገልግሎቱ ዲጂታል መሆኑ ተዓማኒነት ያለው አሰራርን ከመፍጠር ባለፈ የመረጃ ደህንነትን በመጠበቅ አበርክቶው የጎላ ነው ብለዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ እና የክልሉ ፍትህ ትራንስፎርሜሽን ሰብሳቢ ወይዘሮ አስካለች አልቦሮ በበኩላቸው፤ አገልግሎቱ የዜጎችን እንግልት የሚያስቀር እና በተገልጋዩና በመንግስት ተቋማት መካከል ያለውን መተማመን ለማሳደግ ያግዛል ብለዋል። በክልሉ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ጨምሮ ተቋማት በራሳቸው አቅም አሰራራቸውን በማዘመን የዲጂታል አገልግሎት እንዲስፋፋ እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰዋል። በክልሉ የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎትም በቴክኖሎጂ የታገዘ በመሆኑ በቢሮው የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን የሚቀርፍ ነው ያሉት ደግሞ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፍትህ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሙሐመድ ሀሚድ ናቸው። በቀጣይም የዲጂታል አሰራሩን እስከታችኛው መዋቅር በማውረድ ዘርፉን የማዘመን እና አገልግሎት አሰጣጡን የተሳለጠ ለማድረግ እንደሚሰራም አስታውቀዋል።
የኮደርስ ስልጠና የመንግስት አገልግሎትን ለማዘመን አግዟል
Dec 12, 2025 121
አዶላ ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ የኮደርስ ስልጠና የመንግስት አገልግሎትን ለማዘመን እንዳገዛቸው የጉጂ ዞን የመንግስት ሰራተኞች ገለጹ፡፡ በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከወሰዱ የአዶላ ከተማ የመንግስት ሰራተኞች መካከል ወጣት ጉደታ ገመዳ አንዱ ነው፡፡ ስልጠናው ራስን በቴክኖሎጂ በማብቃት ለደንበኞች የተቀላጠፈ አገልግሎትን ለመስጠት ተደማሪ አቅም እንደሚሆን ወጣት ገመዳ ተናግሯል። ከስልጠናው የኮምፒውተር ሳይንስና የሰው ሰራሽ አስተውሎት እውቀትን ማግኘቱ ለስራው ስኬት እንዳገዘው ገልጿል። የወጣት ገመዳን ሀሳብ የሚጋራው ሌላው የከተማው የመንግስት ሰራተኛ ወጣት ደስታ ሀለኬ በበኩሉ ስልጠናው እውቀትና ቴክኖሎጂን በማቀናጀት ተወዳዳሪነቱን እንዳሳደገው ተናግሯል። ስልጠናውን በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት መውሰዱን ገልፆ ስልጠናው የዜጎችን ብቃትና ተወዳዳሪነት በማሳደግ ለተሻለ ስራ የሚያነሳሳ ነው ብሏል፡፡ ይህን እድል በመጠቀም የዘመነ አሰራር ለመተግበር በእውቀትና ክህሎት ለማበልጸግ ሁሉም ሰው ስልጠናውን በመውሰድ ለሀገር ልማት የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባም ልምዱን አካፍሏል፡፡ የዞኑ ሲቪል ሰርቪስ ጽህፈት ቤት የሰው ሀብት ልማትና ስምሪት ቡድን መሪ አቶ ቢሉ ሶርሳ፤ የመንግስት ሰራተኞችን እውቀትና ክህሎት ለማሳደግ 25 ሺህ ሰራተኞች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እንዲወስዱ መታቀዱን ገልጸዋል። ስልጠናው የዲጂታል ኢኮኖሚን ለመገንባት የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ መሆኑን ጠቁመው በእስካሁኑም 23 ሺህ 456 ሰራተኞች ስልጠናውን አጠናቀው የምስክር ወረቀት መውሰዳቸውን ጠቁመዋል፡፡ ስልጠናው የመንግስት ሰራተኞችን ከቴክኖሎጂው ዓለም ጋር በማስተዋወቅ ብቁና ተወዳዳሪ የሚያደርግ አሰራርን እንዲከተሉ ማለሙን አክለዋል፡፡ ይህም በቴክኖሎጂ የተደገፈ ፈጣንና መንግስታዊ አገልግሎት ለመስጠት የሚያግዝ መሆኑንም አመልክተዋል፡፡
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ብልሹ አሠራሮችን አስቀርቷል
Dec 12, 2025 81
አዲስ አበባ፤ታኅሣስ 3/2018 (ኢዜአ)፡-መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ብልሹ አሠራሮችን በመቅረፍ እርካታ በተሞላበት አግባብ አገልግሎቶች እንዲቀርቡ ማስቻሉ ተገለጸ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አሥራት አዳሮ እንዳሉት፤ ማዕከሉ የተንዛዛና ለብልሹ አሠራር የተጋለጠውን የተቋማት አገልግሎት ከብልሹ አሠራር በፀዳ መልኩ ለማቅረብ አስችሏል። ተደራሽ አገልግሎት በመስጠት የዜጎችን እርካታ ማረጋገጥ እና ይባክን የነበረውን የሰው ኃይል፣ ጊዜ፣ ጉልበት ብሎም ሀብት ከብክነት ማዳኑንም ገልጸዋል። በክልሉ ከጥቅምት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአንድ ማዕከል አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑንም አውስተዋል። አገልግሎቱ የተጀመረው በዘጠኝ ተቋማት በ28 አገልግሎት መሆኑን ገልጸው፤ አሁን ላይ አገልግሎቱ ወደ 35 ማደጉን አረጋግጠዋል። ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ጊዜም 3 ሺህ 641 ሰዎች አገልግሎቱን በአንድ ማዕከል ማግኘታቸውን ለኢዜአ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት በአምስት የዞንና የከተማ አሥተዳደሮች መሶብ የአንድ ማዕከልን ለማስፋፋት ጥረት እየተደረገ መሆኑን አመላክተዋል።
የሳይበር ጥቃት ተጋላጭነትን ለመቀነስ...
Dec 12, 2025 157
በአብዛኛው ለጥቃት ተጋላጭ የሆኑት የፋይናንስ ተቋማት እና ባንኮች መሆናቸውን የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር አስገነዘበ። በአስተዳደሩ የሳይበር መከላከል ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር መሀመድ ፈረጃ፤ የፋይናንስ ተቋማት፣ሚኒስቴሮች፣ የሕክምና ተቋማት፣ ዩኒቨርሲቲዎች፣ የቴሌኮም አገልግሎት አቅራቢ ተቋማት፣ የጸጥታና ደኅንነት ተቋማት እንዲሁም ሚዲያዎች በተደጋጋሚ የጥቃት ዒላማ እንደሚደረጉም ተናግረዋል። ስለዚህም የሳይበር ጥቃት ተጋላጭነትን ለመቀነስ ቁልፍ የመሠረተ-ልማት ተቋማትን የሚመሩ አካላት ዘርፉን ወይም ተቋም ተኮር የሳይበር ደኅንነት ፖሊሲዎችን እና ፍሬም ወርኮችን መንደፍ እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል። ከዚህም በተጨማሪ ስታንዳርዶችን እንዲቀርጹ እና አሠራሮች እንዲኖሯቸው ይጠበቃል ነው ያሉት። እነዚህን የአሠራር ሥርዓቶች ወደ መሬት ለማውረድ በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ኃይል እና መሠረተ-ልማቱን ለመጠበቅ የሚያስችል ቴክኖሎጂ እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል። በሰው፣ በአሠራር ሥርዓት እና በቴክኖሎጂ ተቋማት ራሳቸውን ዝግጁ ማድረግ እንዳለባቸውም መክረዋል። የሳይበር ደኅንነትን በተቋማት ለማረጋገጥ ዝቅተኛ የሚባሉትን የደኅንነት መስፈርቶች (Baseline) ማሟላት እና ተግባራዊነታቸውን መከታተል እንደሚጠበቅም አመላክተዋል። ይህንም ለማስቻልም መደበኛ የደኅንነት ዳሰሳና ኦዲት ማከናወን እንደሚጠበቅ ጠቁመዋል። በተጨማሪም ጠንካራ የመከላከል ዐቅም ለመገንባት የ‘ዜሮ ትረስት’ መርኅን ተግባራዊ ማድረግ ይገባል ብለዋል። ይህ ማለትም ቀደም ሲል ስጋት ከውጭ እንጅ ከውስጥ የለም የሚል እንደነበር አውስተው፤ የ‘ዜሮ ትረስት’ መርኅ ግን “ማንንም አለማመን እና ሁሉንም ማረጋገጥ” በሚል የተመሰረት ሲሆን ይህም ስጋት ከውስጥም ከውጭም እንዳለ አምኖ መሥራት ነው ብለዋል። ከላይ ከተገለጹት ጥንቃቄዎች አልፎ የሳይበር ጥቃት ሊያጋጥም እንደሚችል እና የጥቃት ጉዳቱን ለመቀነስ እንዲሁም በጋራ ለመመከት እንዲቻል ከተቋማችን ጋር በቅርበት መሥራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። በአብዛኛው ጊዜ ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭ የሆኑት የፋይናንስ ተቋማት እና ባንኮች መሆናቸውን ዓመታዊ የሳይበር ጥቃት ሪፖርታችን ያመለክታል ብለዋል።
ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ ማዕከል ለመሆን በቁርጠኝነት ትሰራለች
Dec 11, 2025 104
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ ማዕከል ለመሆንና ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከር በቁርጠኝነት እንደምትሰራ የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፖሻል ኢንስቲትዩት ከውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "ለሰላም፣ ለልማት እና ለጋራ ብልጽግና አህጉራዊ አጋርነትን ማጠናከር" በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጁት አዲስ የህዋ ፎረም ተካሂዷል። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አብዲ ዘነበ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢንስቲትዩቱ የኢትዮጵያን ህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማሳደግ እየሰራ ነው። በፍጥነት እያደገ የመጣው የህዋ ሳይንስ በአገራት ልማት አስተዋጽኦው ከፍተኛ መሆኑን አመልክተው፤ በተለይም የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም፣ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ፣ ለሳተላይት ኮሙኒኬሽንና ለሌሎች ስራዎች ማዕከል መሆኑን ገልጸዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ አፍሪካ በህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ ያላት ውክልና በተቀናጀ መልኩ እንዲከናወን እንሰራለን ብለዋል። ኢትዮጵያ ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከርና በስትራቴጂክ ዲፕሎማሲ ግንባር ቀደም ለመሆን ቁርጠኛ መሆኗንም ገልጸዋል። ፎረሙ አዲስ አበባን በህዋ ሳይንስ ዘርፍ የዲፕሎማሲ ማዕከል ለማድረግ ከሚከናወኑ ተግባራት አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል። በኢንስቲትዩቱ የአፍሪካ ጉዳዮች ከፍተኛ ተመራማሪ ግዛቸው አሥራት (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአፍሪካ የህዋ ሳይንስ ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሰላም ግንባታና የብልጽግና ስራዎችን ለማጎልበት በጋራ እንሰራለን ብለዋል። ዲፕሎማሲው በዓለም አቀፍ የህዋ ሳይንስ አስተዳደር የአፍሪካን ጥቅም ለማስጠበቅ፣ ትብብርን ለማጠናከር፣ የተፈጥሮ ሀብቶችን ተደራሽነት ለማጠናከር እገዛ እንደሚያደርግም አብራርተዋል። በዘርፉ ምርምርና መረጃ ልውውጥ በማድረግ የአፍሪካን የጋራ አቅምና ቀጣናዊ ትብብር ማሳደግ እንደሚቻል ተናግረዋል። ኢንስቲትዩቱ የእውቀት፣ የቴክኒክና የአቅም ግንባታ ስራዎች ላይ በጋራ ለመስራት ዝግጁ መሆኑንም ገልጸዋል። የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፖሻል ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ይሽሩን አለማየሁ( ዶ/ር)፤ አዲስ አበባ የአፍሪካ መዲና በመሆኗ ለህዋ ሳይንስ ዲፕሎማሲ ምቹ ናት ብለዋል። አዲስ አበባን በዘርፉ የዲፕሎማሲ ማዕከል ማድረግ በዓለም አቀፍ መድረክ የኢትዮጵያንና የአፍሪካን አቅም ለማሳየት የሚያስችል መሆኑን ነው የገለጹት። በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የጂኦ ስፓሻልና ማኔጅመንት ተጠሪ አንድሬ ኖንጉርማ እንደተናገሩት፤ በህዋ ሳይንስ ዘርፍ የአፍሪካውያንን የጋራ ስራ ማጠናከር ያስፈልጋል። ኢትዮጵያ በዘርፉ ውጤታማ ስራዎች እያከናወኑ ከሚገኙ አገራት አንዷ መሆኗን ጠቅሰው፤ በዘርፉ የመሪነት ሚና ለመወጣት የሚያስችል አቅም እንዳላት ተናግረዋል።
ኢንስቲትዩቱ የባዮቴክኖሎጂ ምርምሮችና ግኝቶችን ለማስተዋወቅ የተቀናጁ ተግባራትን እያከናወነ ነው
Dec 11, 2025 172
ሮቤ ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የባዮቴክኖሎጂ ምርምሮችና ግኝቶችን ለኅብረተሰቡ ለማስተዋወቅ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተቀናጁ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ገለጸ። የኢንስቲትዩቱ የግብርና ባዮ-ቴክኖሎጂ የደቡብ ምሥራቅ መድረክ (ኦፋብ ኢትዮጵያ) ከመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር የባለድርሻ አካላት ዐውደ ጥናት በባሌ ሮቤ አካሂዷል። በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የግብርና ባዮ -ቴክኖሎጂ የኢትዮጵያ አስተባባሪ ታደሰ ዳባ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ በባዮ ቴክኖሎጂ ሳይንስ የግብርናው ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው። ቴክኖሎጂው በግብርናው መስክ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከፍተኛ እገዛ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። ለአብነትም በባዮ ቴክኖሎጂ ሳይንስ በቆሎና የጥጥ ዝርያ ላይ እየተካሄዱ የሚገኙ ምርምሮች ተስፋ ሰጪ ውጤት ማምጣታቸውን አንስተዋል። የባዮቴክኖሎጂ ሳይንስ ጥቅምን በሕብረተሰቡ ዘንድ በአግባቡ እንዲታወቅና ተደራሽ እንዲሆን ተከታታይነት ያለው ግንዛቤ ለመፍጠር ከባለድርሻ አካላት ጋር መሰራቱን አመልክተዋል። የባዮ ቴክኖሎጂ ሳይንስ በተለይ የግብርናው ምርታማነት ላይ ማነቆ የሆኑ የሰብል በሽታዎች፣ አረምና ሌሎች ችግሮችን ለማቃለል የሚያግዝ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት መሪ ተመራማሪ ተስፋዬ ዲሳሳ (ዶ/ር) ናቸው። በሀገሪቱ ባለፉት ዓመታት በቆሎን በማዳቀል ዘርፍ የተካሄዱ የምርምር ሥራዎች በሽታን የሚቋቋምና ምርታማነትን የሚያሻሽል ዘር መገኘቱን አንስተዋል። የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ፣ ምርምርና የቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት በዛብህ ወንድሙ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ሥራ በተጓዳኝ ችግር ፈቺ ምርምሮችን እያካሄደ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በተለይ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የተሻሻሉና የምርጥ ዝርያዎችንና አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በምርምር ተደራሽ ማድረጉን ጠቅሰዋል። የተካሄደው መድረክም የተገኘውን ውጤት ለማሳደግ ጉልህ ድርሻ እንደሚኖረው አንስተዋል። የባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ በተካሄደው የባዮቴክኖሎጂ ዘርፍ መድረክ ላይ የምርምር ውጤቶችና የዘርፉን እምቅ አቅም ለኅብረተሰቡ ለማስተዋወቅ የሚረዱ ሰነዶች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።