ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ለፈጠራ ስራዎች የተሰጠው ትኩረት ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው
Nov 20, 2025 35
አዲስ አበባ፤ ህዳር 11/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት የፈጠራ ስራዎችን ለማበረታታት የሰጠው ትኩረት የልማት ስራዎችን በማገዝ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የተቋማት የስራ ሃላፊዎች ገለፁ። የኢንተርፕርነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀውን ዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሺፕ ሳምንት በማስመልከት ትናንት ውይይት ተካሂዷል።   በመድረኩ መንግስት፣ የግሉ ዘርፍና ስራ ፈጣሪዎች ተቀናጅተው እንዲሰሩ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን በተመለከተ ውይይት ተደርጓል። ሳምንቱ የዘርፉ ተዋንያን ችግር ፈቺ የፈጠራ ውጤቶች ላይ ትኩረት አድርገው እንዲሰሩ ለማበረታታት ያለመ መሆኑም ተገልጿል። በዚሁ ጊዜ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ፤ መንግስት የኢትዮጵያን የኢንተርፕርነርሺፕ ምኅዳር ለማስፋት በከፍተኛ ትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።   ባለፉት ሰባት ዓመታት ሥነ-ምህዳሩን ማስፋት የሚያስችሉ ወሳኝ የአሰራርና የሪፎርም አጀንዎች በመቅረጽ ተግባራዊ ማድረጉን ገልጸዋል። በዚህም ስራ ፈጣሪዎች ከተለምዷዊ አሰራር ተላቀው ንቁ፣ ችግር ፈቺና የስራ ዕድል ፈጣሪ እንዲሆኑ በቅንጅት እየተሰራ ነው ብለዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶር) መንግስት የቴክኖሎጂ ስነ ምህዳሩን ለማስፋት የፖሊሲ፣ ስትራቴጂና የህግ ማዕቀፍ በማዘጋጀት ወደ ስራ መግባቱን አስታውቀዋል።   በዚህም በቅርቡ የጸደቀው የስታርታፕ አዋጅ በዘርፉ ሲያጋጥሙ የነበሩ ችግሮችን በመቅረፍና አዳዲስ እድሎችን በመፍጠር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል ነው ያሉት። የዲጂታል መሰረተ ልማትን ለማስፋፋት በተደረጉ ጥረቶች የዳታ ቤዝና የኢኖቬሽን ኢንኩቤሽን ማዕከላት መገንባታቸውን ጠቅሰዋል። በተሰሩት የዲጂታል መሰረተ ልማት ስራዎች በመታገዝ ሀብት ማፍራት የጀመሩ ስታርታፖች እየተበራከቱ መምጣታቸው ለውጤታማነቱ ማሳያ ነው ብለዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ በረከት ፍስሃፅዮን በበኩላቸው፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት መንግስት የጀመራቸው የልማት ስራዎች ውጤት ማስገኘታቸውን አስታውቀዋል።   በልማት ስራዎች የግል ዘርፉ ሚና እየጨመረ እንዲሄድ እንዲሁም የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን በጋራ ለመፍታት ይሰራል ብለዋል ። የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ኢንስቲትዩት የአካዳሚክ ጉዳዮች ሃላፊ ገነነ አበበ(ዶ/ር) ኢንስቲትዩቱ ለፈጠራና ኢኖቬሽን፣ ችግሮችን ወደ ዕድል ለመቀየርና የማይበገር ሀገራዊ ኢኮኖሚ ለመገንባት እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   ኢንስቲትዩቱ የተለያየ ክህሎት ያላቸው ዜጎች እውቀታቸውን ወደ ተግባር የሚቀይሩበት ምህዳር በማዘጋጀትና ከፋይናንስ ተቋማት በማገናኘት ድጋፍ እንዲያገኙ ማድረጉን ጠቅሰዋል።
የጅማ ከተማ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት አሰጣጥ እንግልትን በማስቀረት ጊዜና ገንዘባችንን ቆጥቦልናል - ተገልጋዮች
Nov 20, 2025 49
ጅማ፤ ህዳር 11/2018(ኢዜአ)፦ የጅማ ከተማ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት አሰጣጥ እንግልትን በማስቀረት ጊዜና ገንዘባቸውን እንደቆጠበላቸው የከተማዋ ተገልጋዮች ገለጹ። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ህዝቡ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ እያነሳቸው የሚገኙ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት የተዘረጋ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አሰራር ነው። አገልግሎት አሰጣጡን አስመልክተው ለኢዜአ አስተያየታቸውን ከሰጡ ተገልጋዮች መካከል አቶ ሞአዝ ጅሀድ በማእከሉ የተገኙት የግብር መለያ ቁጥር ለማውጣት መሆኑን ገልፀው በፍጥነት በመስተናገዳቸው ጊዜ ማትረፋቸውን ተናግረዋል። የተጀመረውን ቀልጣፋ አገልግሎት በማስቀጠል ተገልጋዮች ከአገልግሎቱ ያተረፉትን ጊዜ በልማት ላይ እንዲያውሉት የማድረጉ ተግባር ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል።   የአንድ ማዕከል አገልግሎቱ መረጃን በመፈለግ የሚባክንን ጊዜና የተንዛዛ አሰራርን ያሻሻለ መሆኑን የገለፁት ደግሞ ሌላኛዋ ተገልጋይ ወይዘሮ ኢንዲያ መሀመድ አሚን ናቸው። ከዚህ ቀደም በነበረው አሰራር ረጅም ቀጠሮን ከመስጠት በተጨማሪ አገልግሎቱን በፍጥነት ለማግኘት አዳጋች እንደነበረ አስታውሰው ባገኙት ቀልጣፋ መስተንግዶ መደሰታቸውን ገልጸዋል። ወይዘሮ ካሚላ ጀማል በበኩላቸው የተጀመረው ዘመናዊና ፈጣን የአገልግሎት አሰጣጥ መጠናከር እንዳለበት ጠቁመው ከመረጃ ዴስክ ሰራተኞች እስከ ባለሙያዎች ያለው ቅንጅታዊ አሰራር የተገልጋዩን እርካታ ማሳደጉን መስክረዋል። መንጃ ፍቃድ ለማደስ በአገልግሎት ማእከሉ የተገኘው ወጣት አስረስ ዮሀንስ፤ ዘመናዊ አሰራሩ ቀደም ሲል የነበረውን የተዛዛ አገልግሎት አሰጣጥ በእጅጉ የቀየረው በመሆኑ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብሏል።   የጅማ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ምክትል ስራ አስኪያጅ ጀማል ሳሊ እንዳሉት፤ ዘመናዊ አገልግሎቱ በሰለጠኑ ባለሙያዎችና በቴክኖሎጂ ተደግፎ በተሟላ ሁኔታ እየተሰጠ ነው። የአንድ ማዕከል አገልግሎቱ በ25 መስሪያ ቤቶች ከ130 በላይ በሚሆኑ የተለያዩ የአገልግሎት አይነቶች በቴክኖሎጂ በማስደገፍ እየተሰጠ መሆኑንም አክለዋል። ይህም ብልሹ አሰራርን በማስቀረትና የተገልጋዩን የአገልግሎት እርካታ በማሳደግ ረገድ ተጨማሪ አቅም መፍጠሩንም አቶ ጀማል አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሳይበር ጥቃቶችን አስቀድሞ መመከት የሚያስችል አቅም እየፈጠረ ነው
Nov 20, 2025 62
አዲስ አበባ፤ ህዳር 11/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶችን አስቀድሞ ለመመከት የሚያስችል ጠንካራአቅም በመፍጠር ላይ እንደሚገኝ አስታወቀ፡፡ ባንኩ የሳይበር ደህንነት ወርን ለሁለተኛ ጊዜ እያከበረ ይገኛል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የኮርፖሬት አገልግሎቶች ኤክስኪውቲቭ ምክትል ፕሬዝዳንት ኤፍሬም መኩሪያ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በዲጂታል ልማት ትልቅ ትኩረት ሰጥቷል። ይህን ተከትሎም ባንኩ የ(2020 - 2025) የመጀመሪያ ምዕራፍ ዲጂታላይዜሽን ስትራቴጂውን በተሳካ ሁኔታ አጠናቅቆ ወደ ሁለተኛው ምዕራፍ ዲጂታል መር ስትራቴጂ (2025-2030) መሸጋገሩን ገልፀዋል።   አሁን ላይ ከባንኩ ጠቅላላ ግብይት ውስጥ ከ90 በመቶ በላይ የሚከናወነው በዲጂታል መንገድ መሆኑን ጠቅሰው፤ የግብይት ስርዓቱን ደህንነት ለማስጠበቅ በከፍተኛ ትኩረት እየተሰራ መሆኑንM አረጋግጠዋል። አቶ ኤፍሬም አክለውም የሳይበር ደህንነት አስተዳደርን እስከ ምክትል ፕሬዝዳንት ደረጃ በማሳደግ ባንኩ በሀገር አቀፍ ደረጃ የመጀመሪያው የፋይናንስ ተቋም መሆኑን ገልፀዋል። በተጨማሪም የሳይበር ደህንነት ክፍሎች በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (ኤ.አይ) የሚሠራ የዜሮ ትረስት ደህንነት ስትራቴጂ (Al-powered Zero Trust Security Strategy) መዘጋጀቱን አመልክተዋል። የሳይበር ጥቃትን መከላከል የአንድ አካል ብቻ ተግባር አለመሆኑን ጠቁመውም፤ የሚመለከታቸው አካላት ትብብራቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጠይቀዋል።
በኢትዮጵያ የኢንተርፕርነርሽፕ ስልጠናዎች ችግር ፈቺ የፈጠራ ውጤትና መፍትሔ እያስገኙ ነው
Nov 19, 2025 122
አዲስ አበባ፤ ህዳር 10/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የኢንተርፕርነርሽፕ ስልጠናዎች ችግር ፈቺ የፈጠራ ውጤትና መፍትሔ እያስገኙ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ገለጹ፡፡ የኢንተርፕረነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀውን ዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሽፕ ሳምንት በማስመልከት የውይይት መድረክ እየተካሄደ ነው። ዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሺፕ ሳምንት የዘርፉ ተዋንያን ንቁና ብቁ ተሳትፎ በማድረግ ችግር ፈቺ የፈጠራ ውጤቶች ላይ ትኩረት አድርገው እንዲሰሩ ለማበረታታት ያለመ መሆኑ ተገልጿል። በዚሁ ጊዜ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ፤ መንግስት የኢትዮጵያን የኢንተርፕርነርሽፕ ምኅዳር ለማስፋት በከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ባለፉት ሰባት ዓመታትም የኢንተርፕርነርሽፕ ሥነ-ምህዳሩን ማስፋት የሚያስችሉ የአሰራርና የተቋማት የሪፎርም አጀንዳ በመቅረጽ ወሳኝ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ኢንተርፕርነሪያል መንግስት ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ይህም ከባህላዊ የአሰራር ሥረዓት ጠባቂነት በመላቀቅ ንቁ፣ ችግር ፈቺ እና ዕድል ፈጣሪ መሆን እያስቻሉት መሆኑን ተናግረዋል።   በዚህም መንግስት ውጤታማ የመፍጠንና መፍጠር የአገልግሎት ሥርዓትን በመዘርጋት ስኬት እየተመዘገበ እንደሚገኝ አንስተዋል። የመንግስትን የአሰራር ስርዓት በፈጠራ የታገዘ እንዲሆን የፐብሊክ ሰርቪስ ኢኖቬሽን ላቦራቶሪ በማቋቋም አገልግሎቶችን የማሳለጥ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የኢንተርፕርነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ከተቋቋመ ጀምሮም የኢንተርፕርነር ስልጠና አቅሞችን በማሳደግ በአንድ ጊዜ በርካታ ዜጎችን የማሰልጠን አቅም እየዳበረ መምጣቱን አስረድተዋል። ኢትዮጵያውያን ኢንተርፕርነሮችን በዓለም አቀፍ ውድድሮች ብቁና ንቁ ተወዳዳሪ በማድረግ ሀገራቸውን ከድህነት የሚያወጡ ዜጎችን ማፍራት እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሽፕ ማህበረሰብ አካል እንድትሆንም የኢንተርፕርነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም ባለፈው ዓመት በተደረገው ዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሽፕ ሳምንት ውድድር ላይ ኢትዮጵያ በ8ኛ ደረጃ ማጠናቀቅ አንዳስቻላት አስታውሰዋል። በኢትዮጵያ የኢንተርፕርነር ስልጠናዎች ችግር ፈቺ የፈጠራ ውጤትና መፍትሔ እያስገኙ መሆኑን ነው የተናገሩት። የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሺፕ ሳምንት የፈጠራ አቅሞችን ማጎልበት የሚያስችል መድረክ ነው ብለዋል።
ኢንስቲትዩቱ የኢትዮጵያ ብልጽግና የሚጨበጥና አይቀሬ መሆኑን ያሳየ ነው 
Nov 18, 2025 129
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 9/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በመፍጠርና መፍጠን የኢትዮጵያ ብልጽግና የሚጨበጥና አይቀሬ መሆኑን ያሳየ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትን ጎብኝተዋል፡፡   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና መስሪያ ቤት በዚህ ሳምንት መመረቃቸው ይታወሳል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ከእድሜው በላይ የሚጨበጥ ውጤት ማስመዝገብ የቻለ ተቋም ነው፡፡   የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በመደመር መንግስት ላይ መፍጠር፣ መፍጠንና በዝላይ ማለፍ የሚሉ ጽንሰ ሀሳቦችን በተግባር ያሳየ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ዓለም ከደረሰበት ደረጃ ለመድረስ የግድ ሁሉንም ሂደት ማለፍ አይጠበቅም ያሉት ኃላፊው፤ ነባራዊውን ሁኔታ ታሳቢ በማድረግ በዝላይ ማለፍ ይገባል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ውስጥ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ መሆን የሚያስችላትን አቅም መገንባቷን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የታየው የመፍጠን፣ የመፍጠርና በዝላይ የማለፍ ውጤት የኢትዮጵያ ብልጽግና የሚጨበጥና አይቀሬ መሆኑን ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ፤ ሰው ሰራሽ አስተውሎት በዓለም ላይ ያሉ ሥራዎችን ሁሉ ማከናወን የሚችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡   ሰው ሰራሽ አስተውሎት ሁሉንም ሥራዎች በፍጥነት፣ በጥራትና በግልጸኝነት ማከናወን እንደሚችል ገልጸው፤ ፈጣን ዕድገት ለማስመዝገብ ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ በመዲናዋ ሁሉም ተቋማት ፈጣን አገልግሎት በመስጠት ነዋሪዎች ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ የሚያቀርቡትን ቅሬታ መፍታት የሚያስችል አቅም መገንባቱን ነው የተናገሩት፡፡ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የማያስፈልግበት ቦታ የለም ያሉት ምክትል ከንቲባው፤ የመዲናዋን ፈጣን የአገልግሎት አሰጣጥና ደህንነት ለመጠበቅ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ወንድሙ ሴታ በበኩላቸው፤ የከተማ ሥራ በትክክለኛ መረጃ ላይ የተመሰረተ ሥራ እና ውሳኔ የሚተላለፍበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡   ከዚህም ባለፈ መረጃዎችን ተንትኖ ለቀጣይ የልማት ዕቅዶች ለማዋል፤ እንዲሁም የከተማዋን የክትመት ሁኔታ ለመቆጣጠር ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የተከናወኑ አስደናቂ ሥራዎች መዲናዋን በበቂ የክትመት መረጃ ላይ ተመስርቶ ውሳኔ መስጠት እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡ በመዲናዋ የሚከናወኑ ህገ ወጥ ግንባታዎችን፣ የመሰረተ ልማት እንቅስቃሴዎችንና ቀጣይ ለመስራት የታቀዱትን በመለየት በቂ መረጃ ይሰጣል ብለዋል፡፡ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ኃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጀማሉ ጀንበር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሰው ሰራሽ አስተውሎት የተሳለጠ የመንግስት አገልግሎት በመስጠት የጎላ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡   ከተማ አስተዳደሩ ከኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ማስጀመሩን ገልጸው፤ በቀጣይ በሌሎችም ዘርፎች በጋራ መስራት እንዳለብን አይተናል ብለዋል፡፡ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ሥራዎችን ቀላል ፈጣንና ግልጽ ማድረግ እንደተቻለ በማንሳት፤ ከተማ አስተዳደሩ የጀመረውን የስማርት ሲቲ ግንባታ ለማላቅ በትብብር እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡ በመዲናዋ ዘላቂና ዘመናዊ የመረጃ አያያዝ ስርዓትን በማጎልበት በትክክለኛ መረጃ ላይ የተመሰረተ ሥራ ማከናወን ያስችላል ብለዋል፡፡
መገናኛ ብዙኃን አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የመጠቀም ባህልን የሚያሳድጉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ዘገባዎችን ማጠናከር አለባቸው
Nov 18, 2025 145
አዲስ አበባ፤ሕዳር 9/2018(ኢዜአ)፦መገናኛ ብዙኃን የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የመጠቀም ባህልን የሚያሳድጉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ዘገባዎች ማጠናከር እንደሚኖርባችው የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ገለጸ። የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የልማት ሥራዎች የነገዋን ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት በሚያሳልጥ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ እንድትገኝ ያስቻሉ መሆናቸውን የኢዜአ አመራር አባላት ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) የሥራ ኃላፊዎችና የሙያተኞች ቡድን አባላትም በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና መስሪያ ቤት የቴክኖሎጂ ልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል።   የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና (ዶ/ር)፤ በአጭር ጊዜ ውስጥ 'ኢንተለጀንስ ለሁሉም' በሚል መሪ ሃሳብ በሁሉም ዘርፍ ውጤት እየተመዘገበ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ተቋማትም የዕለት ከዕለት ሥራዎቻቸውን በቀላሉ የሚያከናውኑበት ምቹ የቴክኖሎጂ ምኅዳር እየተፈጠረ እንደሚገኝ አንስተዋል። የበርካታ ዓለም ሀገራት የመገናኛ ብዙኃንና ሌሎች ተቋማት አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን በመጠቀም ጥራትና ፍጥነት ያላቸውን ተግባራትን በማከናወን ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል።   መገናኛ ብዙኃን የኢትዮጵያ ተቋማት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የመጠቀም ባህል የሚያሳድጉበትን ግንዛቤ የሚያሳድጉ የዘገባ ስራዎችን መስራት እንደሚኖርባቸው ገልጸዋል። ይህም ኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የፈጠራ መልካም አጋጣሚዎችን በመጠቀም የሙያተኞችን የሥራ ጫና የሚቀንሱበት ዕድል እንደሚፈጥር አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዋና ስራ አስፈፃሚ ሰይፈ ደርቤ፤ በበኩላቸው በጉብኝቱ ላይ ኢትዮጵያ በዘርፉ በአፍሪካ ከፍ ያለ ስራ ለመስራት ምን እያከናወነች እንዳለች መመልከታቸውን ተናግረዋል።   የኢንስቲትዩቱ ጉብኝታቸውም በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሌሎች መስኮች የኢትዮጵያን የብልጽግና ርዕይ የሚያሳካ ምቹ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መደላድል እየተፈጠረ መሆኑን እንደታዘቡም ገልጸዋል። በኢንስቲትዩቱም ታዳጊዎች የኢትዮጵያን መፃኢ እጣ ፋንታ በተሻለ ጉዞ ማጀብ የሚያስችል የፈጠራ ሥራ እያከናወኑ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዚህም ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሀገራት ከውጭ የሚገባን ቴክኖሎጂ ብቻ የመጠቀም ባህል በመቀየር ለአህጉሪቷ ጭምር በአርዓያነት የሚጠቀስ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ፈጠራ ስራዎች እያከናወነች እንደምትገኝ መመልከታቸውን ጠቅሰዋል።   በጉብኝቱ የተሳተፉ የኢዜአ አመራር አባላትም፤ ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ውስጥ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ለአፍሪካዊያን ጭምር ትምህርት የሚሰጥ አመርቂ ስኬት ማስመዝገቧን እንደታዘቡ ገልጸዋል።   በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የፈጠራ ሙያተኛን ለማፍራት የሚከናወኑ ተግባራትም የነገዋን ኢትዮጵያ የተሻለ ማድረግ በሚያስችል የትልም ጉዞ ላይ መሆኗንም ተናግረዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኅዳር 07/2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና መሥሪያ ቤት ሕንፃን መርቀው ስራ ማስጀመራቸው ይታወሳል።
የአፍሪካን ዘላቂ ብልጽግና ለማረጋገጥ ለክህሎትና ፈጠራ ከፍተኛ ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል
Nov 18, 2025 166
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 9/2018(ኢዜአ)፦የአፍሪካን ዘላቂ ብልጽግና ለማረጋገጥ ምርታማነትን ማሳደግ፣ ለቴክኖሎጂ፣ ለክህሎትና ፈጠራ ከፍተኛ ትኩረት መስጠት እንደሚገባ ተገለጸ፡፡ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የግሉ ዘርፍ ልማት፣ ቀጣናዊ ውህደት፣ ንግድ፣ የመሰረተ ልማት፣ ኢንዱስትሪ እና ቴክኖሎጂ ኮሚቴ አራተኛው ስብሰባ መካሄድ ጀምሯል፡፡ መደበኛ ስብሰባው "ለዘላቂ እና አሳታፊ ዕድገት ቀጣናዊ ውህደትን ለማሳደግ የዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን እና ፈጠራን መጠቀም" በሚል መሪ ሃሳብ ለሁለት ቀናት ይካሄዳል፡፡ በውይይቱ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችና ፈጠራ የአፍሪካን ቀጣናዊ ትስስርና ዘላቂ ዕድገት ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡   የተመድ ምክትል ዋና ጸሐፊና የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክላቨር ጋቴቴ ባደረጉት ንግግር፤ አፍሪካ በአህጉራዊ ውህደትና በፈጠራ ላይ በመመስረት ዓለም አቀፍ ፈተናዎችን ወደ ዕድል መለወጥ ይገባታል ብለዋል፡፡ ዓለም በፈጣን የቴክኖሎጂ ዑደት፣ የጂኦ-ፖለቲካ ውጥረት እና የአየር ንብረት ለውጥ ተግዳሮቶች ላይ እንደምትገኝ አንስተዋል፡፡ አፍሪካ በርካታ ታዳሽ ኃይሎች ያሏት መሆኑን የገለጹ ሲሆን በቅርቡ ተግባራዊ ያደረገችውን የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ጨምሮ ተወዳዳሪ የማይገኝላቸው ሃብቶች መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ አፍሪካ ፈጠራን በመጠቀም የሞባይል ገንዘብ ዝውውር እና መድኃኒት የሚያደርሱ ድሮኖችን በመስራት ለፈተናዎቿ ምላሽ መስጠት መጀመሯን በበጎ አንስተዋል፡፡ የሰው ሰራሽ አስተውሎት በዓለም አቀፍ ደረጃ ምርታማነትን በዓመት እስከ 40 በመቶ ሊያሳድግ እንደሚችል ጠቅሰው፤ አፍሪካ ይህን ማስፋፋት ይጠበቅባታል ብለዋል፡፡   በአፍሪካ ለመሰረተ ልማት ግንባታ ከፍተኛ ትኩረት መስጠት እንደሚገባ ጠቁመው፤ ድንበር ተሻጋሪ የሆነ የዲጂታል ቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ግንባታ ላይ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከአባል ሀገራትና ከአጋሮች ጋር በመተባበር የበለጸገች አፍሪካ ለመገንባት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ጠቁመዋል፡፡ የግሉ ዘርፍ ልማት፣ ቀጣናዊ ውህደት፣ ንግድ፣ የመሰረተ ልማት፣ ኢንዱስትሪ እና ቴክኖሎጂ ኮሚቴ ሊቀ-መንበር ማማድጃም ዲኒስ ድጃሎ በበኩላቸው፤ አፍሪካ ዘላቂ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ምርታማነትን ማሳደግ፣ በቴክኖሎጂ፣ በክህሎትና በፈጠራ ላይ ማተኮር አለባት ብለዋል፡፡   ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች እሴትን የሚጨምሩና ተወዳዳሪነትን የሚያሳድጉ በመሆናቸው በስፋት መጠቀም እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡ ለአፍሪካ ዘላቂ ዕድገትና ብልጽግና ምርታማነትን በፈጠራ ማሳደግ እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል የዲጂታል ጤና አገልግሎትን የማስፋት ተግባር እየተከናወነ ነው - ቢሮው
Nov 18, 2025 99
አዳማ፤ ህዳር 9/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የዲጂታል ጤና አገልግሎትን በሁሉም የህክምና ተቋማት በማስፋት ቀልጣፋ ህክምና ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። በዲጂታል ኢትዮጵያ ስትራቴጂ በግልጽ እንደተመላከተው የመንግስት አገልግሎቶችን በማዘመን የዲጂታል ጤናን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶን ማስፋት አንዱ ተግባር ነው። የጤናውን ዘርፍ አገልግሎት ዲጂታላይዝ ለማድረግ ሲስተሞችን ማበልጸግ፣ የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን(ICT) መሰረተ ልማቶችን መዘርጋት፣ የዲጂታል አስተዳደርን ማስፈን እንዲሁም የአሰራር ስርዓት በማዘጋጀት በሀገር አቀፍ ደረጃ መተግበር ዋና ዋና ስራዎች ናቸው። የኦሮሚያ ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዶክተር ተስፋዬ ክበበው ለኢዜአ እንዳሉት የዲጅታል ጤና ስርዓት የጤና አገልግሎትን ቀልጣፋ፣ ጥራቱን የጠበቀና አስተማማኝ ማድረግ ያስችላል። ለዚህ እውን መሆን በክልሉ በተመረጡ ሆስፒታሎች ከወረቀት ነፃ የሆነው የዲጂታል ጤና አገልግሎት በፓይለት ደረጃ ተተግብሮ ውጤታማ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የጤና አገልግሎት አሰጣጡን ግልጽ፣ ተደራሽና ቀልጣፋ ለማድረግ እና እንደ ሀገር ለተጀመረው የዲጂታላይዜሽን ጉዞ ትልቅ ምዕራፍ እየከፈተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት አገልግሎቱን በክልሉ በሚገኙ ሁሉም ሆስፒታሎች፣ ጤና ጣቢያዎችና ጤና ኬላዎች ደረጃ ለማስፋት እየተሰራ መሆኑንም አብራርተዋል።   የቢሾፍቱ አጠቃላይ ሆስፒታል ሥራ አስኪያጅ ዶክተር ታደሰ ጎንፋ በበኩላቸው ሆስፒታሉ ለሶስት ሚሊዮን ህሙማን አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ ገልጸው ሁሉም ዓይነት የህክምና አገልግሎት ሙሉ በሙሉ ዲጂታላይዝ አድርገናል ብለዋል። ይህም የታካሚዎችን እንግልት በመቀነስ ተገልጋዮች በቀላሉ ከሐኪሞቻቸው ጋር እንዲናበቡ በማድረግ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ አድርጓል ነው ያሉት።   የዲጂታል ጤና አገልግሎቱ መተግበር ለህሙማን ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲሰጥ ከማድረጉም ባሻገር የተገልጋዮችን እንግልት ቀንሷል ያሉት ደግሞ የጊኒር አጠቃላይ ሆስፒታል ሥራ አስኪያጅ ኑር ዛላም ናቸው። ዲጂታል ጤና በዘመናዊ አሰራር ለውጥ እያመጡ ካሉ ግንባር ቀደም ዘርፎች መካከል ተጠቃሽ መሆኑንም አመላክተዋል። በአሁኑ ወቅት ሆስፒታሉ ሁለት ሚሊዮን ለሚሆኑ ተገልጋዮች አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ተናግረው የዲጂታል ጤና ስርዓት መዘርጋቱ አገልግሎቱን ቀልጣፋና ውጤታማ አድርጎታል ብለዋል።
የመንግስት አገልግሎትን በቴክኖሎጂ በመታገዝ ለመስጠት የተጀመረው ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል
Nov 17, 2025 180
አዲስ አበባ፤ ህዳር 8/2018(ኢዜአ)፦ የመንግስት አገልግሎትን በቴክኖሎጂ በመታገዝ ለመስጠት የተጀመረው ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሃብት ልማት ስራ ስምሪት እና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። ቋሚ ኮሚቴው የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴርን የ2018 በጀት ዓመት የመጀመርያው ሩብ ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ገምግሟል፡፡ ሚኒስቴሩ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግ፣ በዲጂታል መታወቂያና በኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና አበረታች ተግባራትን በማከናወን ላይ ይገኛል፡፡ በኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ሂደት ከተቋማት ጋር በመቀናጀት የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ስራዎች በማከናወን ላይ ነው።   ቋሚ ኮሚቴው ሚኒስቴሩ በቴክኖሎጂ የተደገፉ የመንግስትና የንግድ አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል አስቻይ ሁኔታ በመፍጠር ሀገራዊ ኢ-ኮሜርስና የኢንተርኔት የንግድ ግብይት ስርዓትን ለማሳደግ ምን እየሰራ እንደሆነ ጥያቄ አቅርቧል። የኢትዮ-ኮደርስ መሰረታዊ የዲጂታል ክህሎት ስልጠና ለመስጠት የሚኒስቴሩ ድጋፍና ክትትል ምን ይመስላል በሚለው ላይም ማብራሪያ ጠይቋል።   የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) የተቋማቸውን አፈጻጸም ባቀረቡበት ወቅት እንዳስታወቁት፤ ባለፉት ሶስት ወራት በዘርፉ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል ብለዋል፡፡ በዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ከተቋማት ጋር በመቀናጀት የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ስራዎች መከናወናቸውን በመግለጽ። በዚህም 10 የንግድ ተቋማት ወደ ኤሌክትሮኒክ ግብይት መግባታቸውን፣ ሶስት የኤሌክትሮኒክ ግብይት ማሳለጫ ፕላት ፎርሞችን በማዘጋጀት ለ56 አይሲቲና ዲጂታል ኢንዱስትሪዎች ብቃት ማረጋገጫ መስጠት መቻሉን ጠቅሰዋል።   በሌላ በኩል በኦንላይን የሚሰጡ የመንግስት አገልግሎቶችን በሚመለከት የተያዘውን ዕቅድ ሙሉ በሙሉ ማሳካት መቻሉንም አስታውቀዋል። ከዲጂታል መታወቂያ ጋር በተያያዘ በ2018 የመጀመርያ ሩብ ዓመት አምስት ሚሊዮን ተጠቃሚዎች አገልግሎቱን ማግኘታቸውን ጠቁመዋል። በኢትዮ-ኮደርስ መሰረታዊ የዲጂታል ክህሎት ስልጠና ባለፉት ሶስት ወራት ከ ሁለት ነጥብ አራት ሚሊዮን በላይ ሰዎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው ሚኒስትር ዴኤታው ያነሱት። ከተሞችን በዲጂታል አድራሻ ስርዓት ለማካተት በርካታ ስራዎች መሰራታቸውን ጠቅሰው፤ በሩብ ዓመቱ የአምስት ከተሞች ትግበራን የማጠናቀቅ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። ሀገራዊ ኢኖቬሽን ምርምርና ቴክኖሎጂን በሚመለከት በሩብ ዓመቱ ከዕቅድ በላይ አፈጻጸም መመዝገቡን ነው ያስታወቁት፡፡   እንዲሁም 205 ችግር ፈቺ ምርምሮችን በምርምር እና በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ማከናወን መቻሉንም አንስተዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሃብት ልማት ስራ ስምሪት እና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር)፤ ሚኒስቴሩ ችግር ፈቺ ምርምሮችን በማድረግ የተቋማትንና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባ አሳስበዋል። የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አበረታች መሆኑን ጠቅሰው፤ ተቋማት በቴክኖሎጂ የተደገፈ አገልግሎት እንዲሰጡ በቅንጅት መስራት ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። ኢትዮጵያ ወደ ኢንዱስትሪ ለመሸጋገር በምታደርገው ጉዞ ቴክኖሎጂ አስፈላጊ በመሆኑ ከግብርና ሚኒስቴር ጋር የሚደረገው ቅንጅታዊ አሰራር ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ነው ያስገነዘቡት። ተቋማት ሰው ሰራሽ አስተውሎትን ለመጠቀም ዝግጁ እንዲሆኑ ማገዝ እንደሚገባ አሳስበው፤ ቴክኖሎጂውን አስመልክቶ ለተቋማትና ለማህበረሰቡ ግንዛቤ መፍጠር እንደሚያስፈልግም ጠቁመዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶር) በመጨረሻም በቋሚ ኮሚቴው የተነሱ ክፍተቶችን ለመፍታት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት በትኩረት እንሰራለን ሲሉ አረጋግጠዋል፡፡
በኢትዮጵያ ኢንተርፕርነርሽፕን የመንግስት መለያ ማድረግ የሚያስችሉ ተቋማትና ሕጎች ተተግብረዋል - ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Nov 17, 2025 145
አዲስ አበባ፤ ህዳር 8/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ባለፉት ሰባት ዓመታት ኢንተርፕርነርሽፕን የመንግስት መለያ ማድረግ የሚያስችሉ ተቋማትና ሕጎች መተግበራቸውን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። የኢንተርፕርነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ጠባቂነትን አስወግዶ በሀሳብ ሀብት መፍጠር እንደሚቻል ያሳየ ተቋም መሆኑንም ጠቅሰዋል። የኢንተርፕርነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴርና ዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሽፕ ሳምንት በኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ዓለም አቀፍ የኢንተርፕርነርሽፕ ሳምንት "በጋራ እንገንባ" በሚል መሪ ሀሳብ ተከፍቷል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የኢንተርፕርነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ሀሰን ሁሴን(ዶ/ር)፣ ዲፕሎማቶችና ሌሎች ተሳታፊዎች በመክፈቻ መርሀ ግብር ላይ ተገኝተዋል። ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በዓለም አደባባይ ስሟን ከፍ ያደረጉ አንቱ የተባሉ ምስጉን፣ ታታሪ ኢንተርፕርነሮችስ ስትፈጥር ቆይታለች።   ይሁን እንጂ ኢትዮጵያ ኢንተርፕርነርሽፕን የመንግስቷ መለያ ማድረግ የሚያስችሉ ተቋማትን የገነባችው፣ ሕጎችን ያወጣችው ባለፉት ሰባት ዓመታት ነው ብለዋል። በተለይም ባለፉት አራት ዓመታት የኢንተርፕርነርሽፕ ሥነ ምህዳርን ተቋማዊ ማድረግ የሚያስችል እንቅስቃሴ መደረጉን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የሀሳብ ብዝሃነት ጸጋ ለሀሳብ ፈጠራ ወሳኝ መሆኑን በማንሳት፤ የኢንተርፕርነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ጠባቂነትን አስወግዶ በሀሳብ ሀብት መፍጠር እንደሚቻል በተግባር አሳይቷል ነው ያሉት። በዚህም ባለፉት ሰባት ዓመታት በኢትዮጵያ ኢንተርፕርነርሽፕን የመንግስት መለያ ማድረግ የሚያስችሉ ተቋማትና ሕጎች ተተግብረዋል ብለዋል። ኢትዮጵያ የኢንተርፕርነሮች መፍለቂያ ትሆናለች ያሉት ሚኒስትሯ፤ መንግሥት የኢንተርፕርነርሽፕ ምህዳሩን ምቹ ማድረጉን ገልጸዋል። ሀሳብ ካለ ሀብት መፍጠር እንደሚቻል አምናለሁ ያሉት ሚኒስትሯ፤ ይህን ተግባራዊ ማድረግ የሚያስችል እምቅ ሀገራዊ አቅም፣ ፖሊሲና ተቋም ተገንብቷልም ብለዋል። የመደመር መንግሥት ኢትዮጵያ ኢንተርፕርነር መሆንና እንዴት እንደምትሆን በግልጽ አስቀምጧል ነው ያሉት።   የኢንተርፕርነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ሀሰን ሁሴን(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የኢንተርፕርነርሽፕ ሁነቶችን በማዘጋጀት ብራዚልን በመቅደም ከዓለም አንደኛ ሆናለች ብለዋል። ኢንተርፕርነሮች የፈጠራ መፍትሔዎችን ወደ መሬት የሚቀይሩ፣ ምኞትን የሚያሳኩ፣ አይቻልምን ችለው የሚያሳዩ ፈር ቀዳጅ ባለራዕዮችና ከዋኞች ናቸው ነው ያሉት። ኢንተርፕርነሮች ሀገር ሰሪዎች መሆናቸውን ጠቁመውም በዘንድሮው 12ኛው የኢንተርፕርነርሽፕ ሳምንት ስልጠናዎች፣ የፈጠራ ሀሳብ ውድድሮችና ጥናቶች ይከናወናሉ ብለዋል። በኢትዮጵያ የሚወሰን ሳይሆን ድንበር ተሻጋሪ ሥራ ጀምረናል ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የመጨረሻ ግባችን አይበገሬ ማህበረሰብ፣ ዜጋና ሀገር መገንባት ነው ሲሉም ገልጸዋል።
የአገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Nov 17, 2025 136
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 8/2018 (ኢዜአ)፡-በአፋር ክልል ያለውን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ ገለጹ። የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ የክልሉን መሶብ (ኮራ) የአንድ ማዕከል አገልግሎት በሰመራ ሎጊያ ከተማ ስራ አስጀምረዋል። በመርኃ ግብሩ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ፣ የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር መኩሪያ ሀይሌ (ዶ/ር) እንዲሁም የፌደራል እና የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች ተገኝተዋል።   የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ በዚሁ ወቅት፤ ለአገልግሎቱ መጀመር አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት ምስጋና አቅርበው፤ በቀጣይ በተለያዩ የክልሉ ከተሞች መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ለማስፋፋት እንደሚሰራ ተናግረዋል። በክልሉ ያለውን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል፡፡ 10ኛው የከተሞች ፎረም በሰመራ ሎጊያ ከተማ መከናወኑ ለከተማዋ ከፍተኛ መነቃቃት የፈጠረ መሆኑንም ጠቁመዋል። የከተማ እና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በበኩላቸው፤ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ለከተሞች ብዙ ትርጉም አለው ብለዋል።   አገልግሎቱ ዜጎች የሚገባቸውን አገልግሎት በተቀላጠፈ ሁኔታ የሚያገኙበት መሆኑን ጠቅሰው፤ በሰመራ ሎጊያ የተገነባው የመሶብ ማዕከል የሚደነቅ ስራ መሆኑን ጠቁመዋል። ማዕከሉ መልካም አስተዳደርን በማስፈን በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ከፍተኛ ለውጥ እንደሚያመጣ ተናግረዋል። በተጨማሪም በአንድ ቦታ በርካታ አገልግሎት በመስጠት ለዜጎች እፎይታን የሚሰጥ መሆኑን ጠቁመዋል።   መሶብ የተሳለጠ ሰው ተኮር አገልግሎት የሚሰጥበት ማዕከል መሆኑን የገለጹት ደግሞ የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ሀይሌ(ዶ/ር) ናቸው።   የመልካም አስተዳደር ችግሮችን የሚፈታ እንዲሁም የአገልግሎት ልህቀት ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል። ማዕከሉ ዜጎች ከመንግስት የሚፈልጉትን አገልግሎት በተቀላጠፈ ሁኔታ የሚያገኙበት የኢትዮጵያ ማንሰራራት መገለጫ መሆኑን ተናግረዋል። የአፋር ክልል በዚህ ረገድ ያቋቋመው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የሚደነቅ ስራ መሆኑን ገልጸው ኮሚሽኑ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በአፍሪካ በከፍተኛ ደረጃ የሚታይ ተቋም ነው 
Nov 17, 2025 109
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 8/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በአፍሪካ በከፍተኛ ደረጃ የሚታይ ተቋም መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና መሥሪያ ቤቱን ቀድሞ ከነበረበት ቀይሮ ወደ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የቀድሞ ሕንፃ በተዛወረበት ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) መልዕክት አስተላልፈዋል። በዚሁ ወቅትም የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በአምስት ዓመት ውስጥ አሁን በሚገኝበት ደረጃ ላይ መድረሱ የሚደነቅ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በአፍሪካ በከፍተኛ ደረጃ የሚታይ ተቋም መሆኑን ገልጸው፤ የሮቦቶችን ሶፍትዌር ብቻ ሳይሆን ውጫዊ የአካል ክፍልን (ሃርድዌር) መሥራት ጀምሯል ብለዋል። ድሮን ማምረት ብቻ ሳይሆን የማነጋገር ዐቅም እየፈጠረ ያለ ተቋም መሆኑንም ተናግረዋል።   አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ በአፍሪካ ደረጃ የሚወዳደር አሠራርን የሚከተል መሆኑን ጠቁመው፤ በርካታ ምርቶችን አውጥቷል ብለዋል። በጤናው ዘርፍ የጡት ካንሰር ልየታ ላይ ትልቅ ውጤት ማምጣት መቻሉን እና ይህም በዓለም አቀፍ ደረጃ በአርቲፊሻል ዐዋቂዎች ዘንድ ተቀባይነት ብሎም የባለቤትነት መብት ያገኘ ሥራ ነው ብለዋል። በግብርና ዘርፍም የቡናና የሌሎች አዝርዕቶች በሽታ የሚለይ ፕሮዳክት መመረቱን በመጠቆም ለዚህም ባለቤትነት መብት መኖሩን አስረድተዋል። በሌላ በኩል መሶብ የሚባለውን በአንድ ማዕከል ከ100 በላይ አገልግሎቶች የሚሰጠውን ሲስተም የገነባው አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት መሆኑን አስታውቀዋል። ገንዘብ ሚኒስቴር፣ገቢዎች ሚኒስቴር እና ጉምሩክ ኮሚሽንን ጨምሮ ተቋማት አሠራሮቻቸውን ለማዘመን የሚገለገሉባቸው በርካታ ሲስተሞችን መገንባት መቻሉን አንስተዋል። የኢንስቲትዩቱ ሞቶ ኤ አይ ለሁሉም ስለሆነ፤ ከዚህ አንጻር አንዱ ማሳያ ክላውድ ኮምፒቲንግ መሆኑን አንስተዋል።   ለምሳሌ ከዳታ አጠቃቀም ጋር ተያይዞ አማርኛ፣ አፋን ኦሮሞ፣ ሶማሊኛ፣ ትግርኛ እና አፋርኛ የአንዱ ቋንቋ ተናጋሪ ሦስተኛ ሰው ሳያስገባ ከሌላኛው ቋንቋ ተናጋሪ ጋር መግባባት የሚችልበትን መንገድ፣ በጽሑፍ የገባን መልዕክት ወደ ድምጽ የመቀየር፣ በድምጽ ያለ መልዕክትን ወደ ጽሑፍ የመቀየርና መሰል አገልግሎት ለመስጠት በሺህ ሰዓቶች የሚቆጠሩ ኦዲዮዎችን ዳታዎች በማስገባት እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። የግብርና ሪቮሉሽን አንድ ሁለት ሦስት እያለ መጥቷል እኛ እዛ ውስጥ አልነበርንም፤ ቴክኖሎጂካል ሪቮሉሽን ነበሩ፣ ኢንደስትሪያል ሪቮሉሽኖች ነበሩ፤ በእነዚህ ሁሉ ኢትዮጵያ በሬና ሰውን ማላቀቅ ሳትችል የኖረችበት ዋናው ምክንያት አዲስ ዕውቀት፣ አዲስ ልምምድ፣ አዲስ ፈጠራ ሲፈጠር ያንን ነገር ለማወቅና ለመከተል የነበረው ጉጉት፣ ዝግጁነት እና እሳቤ አናሳ ስለነበረ ነው ሲሉ ገልጸዋል። እዚህ ላይ ለመተካከል ሳይሆን ጥሩ ተከታይ ለመሆን እንኳ በእጅጉ ይቀረን ነበር ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሁን ሁኔታው መቀየሩን በአጽንኦት አስረድተዋል። ስለዚህ ብንፈልግም ባንፈልግም ራሳችንን በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ሂደት ውስጥ ማስገባት ካልቻልን ደረጃው የትም ቦታ ይሁን እንደ ሀገር እንደ ከዚህ ቀደሙ ከትላልቅ ሪቮሉሽኖች ወደ ኋላ እንቀራለን ሲሉ አስገንዝበዋል።
ፎረሙ ከተሞች የቴክኖሎጂ መፍለቂያ መሆናቸው በተግባር የታየበት ነው 
Nov 17, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 8/2018 (ኢዜአ)፡-10ኛው የከተሞች ፎረም ኤግዚቢሽን በመደመር መንግሥት ከተሞች የቴክኖሎጂ እውቀት መፍለቂያ መሆናቸው በተግባር የታየበት መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ። 10ኛው የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም "የከተሞች ዕድገት ለኢትዮጵያ ልህቀት” በሚል መሪ ሀሳብ በአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል፡፡ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ 10ኛውን የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም ኤግዚቢሽን ማስጀመራቸው ይታወሳል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትሯ ጫልቱ ሳኒ ፎረሙን አስመልክቶ የተዘጋጀውን ኤግዚቢሽን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።   ሚኒስትሯ ጉብኝታቸውን አስመልክቶ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ በኤግዚቢሽኑ በከተሞች ያለውን ከፍተኛ መነቃቃት በተጨባጭ ማየት መቻላቸውን ገልጸዋል። አውደ ርዕዩ የዜጎች የስራ ባህል እየተቀየረ መምጣቱ በጉልህ የታየበት መሆኑን ጠቁመው ፤ መንግስት ለከተሞች የሰጠው ትኩረት በተጨባጭ ውጤት እየተረጋገጠ መምጣቱን ተናግረዋል። ከተሞች ባላቸው አቅም እና ጸጋ እየለሙ መሆናቸውን ያነሱት ሚኒስትሯ ኤግዚቢሽኑ የከተሞች የእርስ በእርስ ግንኙነት እንዲጠናከርና ምርጥ ተሞክሮዎችን እንዲለዋወጡ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ነው የገለፁት።   ኤግዚቢሽኑ የበለጠ መተዋወቂያ መድረክ ከመሆኑ ባለፈ ከተሞች የተለያዩ የፈጠራ ውጤቶቻቸውን ያሳዩበት መሆኑን ተናግረዋል። ኤግዚቢሽኑ በመደመር መንግሥት ከተሞች የቴክኖሎጂ እውቀት መፍለቂያ መሆናቸው በተግባር የታየበት መሆኑን አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያን ብቃት እና ዐቅም በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዐይቻለሁ- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Nov 17, 2025 98
አዲስ አበበ፤ሕዳር 8/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያን የማድረግ ብቃት እና ዐቅም በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዐይቻለሁ ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና መሥሪያ ቤቱን ቀድሞ ከነበረበት ቀይሮ ወደ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የቀድሞ ሕንፃ በተዛወረበት ወቅት ጠቅላይ ሚኒስትሩ መልዕክት አስተላልፈዋል። በመልዕክታቸውም፥ በአጠቃላይ ዛሬ ያየሁት ነገር ሰው የጠራ ራዕይ ካለው፣በከፍተኛ ዲሲፕሊን የሚሠራ ከሆነ አንድን ነገር ባየው ልክ ማሳካት እንደሚችል ነው ብለዋል።   ሁሉ ነገር እየተከናወነ ያለው በኢትዮጵያውን በመሆኑ ኢትዮጵያ የማድረግ ብቃት ያላት ሀገር እንደሆነች ዐይቻለሁ ብለዋል። ያሉን ሕንጻዎችና ስፍራዎች ይሁነን ብለን አስበን ብንሠራቸው እጅግ ያማሩ መሆን እንደሚችሉም ተመልክቻለሁ ነው ያሉት። የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን በተቋም ደረጃ ካስጀመርነው አምስት ዓመት ገደማ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሁን ላይ የተቋም ግንባታ ሥራው እጅግ አስደማሚ መሆኑን ተናግረዋል። ራዕይ እና ዲሲፕሊን ሲገናኙ ምን ዓይነት ነገር መፍጠር እንደሚቻል ይህ ተቋም ማሳያ መሆኑን ጠቅሰዋል። አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በመሥሪያ ቦታ ብቻ እንኳን ቢወሰድ ለኢትዮጵያ ዐይን ገላጭ፣ አዲስ ምልከታ፣ አዲስ ዕይታን የሚገልጥና የሚያሳይ በጣም ለሥራ የተመቸ ወጣቶች ረዥም ሠዓት ሊሠሩ የሚችሉበት ተቋምና ሥፍራ ሆኗል ሲሉም ገልጸዋል።   የዛሬ አምስት ዓመት አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የሚለውን ሐሳብ ስናነሳ ተቋም ይፈጠር ሲባል በእኛም ውስጥ ብዙዎች በቀላሉ የገዙት ሐሳብ አልነበረም ሲሉም አውስተዋል። ነገር ግን አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የሰው ልጅ የሚያስብበትን መንገድ፣ኢማጅን የሚያደርግበትን መንገድ፣ ፖሲብሊቲን የሚያይበትን መንገድ እየቀረጸ መጥቷል ሲሉም አብራርተዋል።
ኢንስቲቲዩቱ በጤና፣ በግብርና፣ በአገልግሎት ዘርፍ እያደረገ ያለው የመሪነት አስተዋፅኦውን እየተወጣ ነው -   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Nov 16, 2025 100
አዲስ አበባ፤ ህዳር 7/2018(ኢዜአ)፦ ኢንስቲቲዩቱ በጤና፣ በግብርና፣ በአገልግሎት ዘርፍ እያደረገ ያለው የመሪነት አስተዋፅኦውን እየተወጣ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። በክላውድ ኮምፒውቲንግ፣ ትላልቅ የመረጃ ቋቶች፣ የመረጃ ፍለጋ፣ ሮቦቲክስ እና ኢመርሲቭ ቴክኖሎጂዎች አቅሙን በማጎልበት ላይ ይገኛል ሲሉም በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት አስታውቀዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም የኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ጽሕፈት ቤቱን ቀድሞ ከነበረበት በመለወጥ መሃል ከተማ ወደ ቀድሞው የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ሕንፃ አዛውሯል ብለዋል።   በአንድ አመት ጊዜ ውስጥ አስደናቂ የግንባታ ለውጥ እና ዘመናዊ የመሥሪያ ሥፍራ ጥበብን በማሳየት ለሠራተኞቹ እጅግ ምቹ የሆነ ስፍራንም መፍጠር ችሏል ነው ያሉት። ተቋሙ በአምስት አመታት ጊዜ ውስጥ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ሕይወታችንን በፍጥነት በመቅረጽ ውስጥ ያለውን ስፍራ በሚያንፀባርቅ እና ሀገራችንም በዚህ አለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ውድድር በንቁነት መሳተፏን በሚያረጋግጥ መንገድ ከፍታ ላይ ደርሷል ብለዋል። ኢንስቲትዩቱ በጤና፣ በግብርና፣ በአገልግሎት ዘርፍ እያደረገ ያለው የመሪነት አስተዋፅኦውን እየተወጣ ሲሆን በክላውድ ኮምፒውቲንግ፣ ትላልቅ የመረጃ ቋቶች፣ የመረጃ ፍለጋ፣ ሮቦቲክስ እና ኢመርሲቭ ቴክኖሎጂዎች አቅሙን በማጎልበት ላይ ይገኛል ነው ያሉት።   በቅርቡ የተጀመረው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ስታርት አፕ መዐከል ደግሞ ይኽንን ከባቢ የበለጠ ያጠናክረዋል ብለዋል በመልዕክታቸው። ዜጎች ሀሳብ ብቻ ይዘው በመምጣት ፕሮቶታይፕ ለመፍጠር፣ ለማባዛት ብሎም ከግሉ ዘርፍ ኢንቬስተሮች ጋር እንዲገናኙ እድል ያመቻቻል። እስከ አሁን 200 ሀሳብ ፈጣሪዎች በዚህ እድል ተጠቅመዋል ሲሉም አስታውቀዋል።
መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ለከተሞች አገልግሎት አሰጣጥ መዘመን ትልቅ እገዛን የሚያደርግ ነው 
Nov 16, 2025 119
አዲስ አበባ፤ ህዳር 7/2018(ኢዜአ)፦መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ለከተሞች አገልግሎት አሰጣጥ መዘመን ትልቅ እገዛን የሚያደርግ መሆኑን የኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ሀይሌ (ዶ/ር) ገለጹ። 10ኛው የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም "የከተሞች ዕድገት ለኢትዮጵያ ልህቀት” በሚል መሪ ሀሳብ በአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያ ከተማ መካሄድ ጀምሯል፡፡ በሁለተኛው ቀን ውሎም "የኢትዮጵያ የፐብሊክ ሰርቪስ ሪፎርም እና መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት" በሚል የፓናል ውይይት ተካሂዷል። የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ሀይሌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የመንግስት አገልግሎት እና አስተዳደር ሪፎርም የተነደፈው ለሁሉም ሴክተር ነው።   እንዲሁም ዘመን ተሻጋሪ ተቋማት መገንባትን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ እሳቤው የሰራተኛን የአቅም ክፍተቶችን በመለየት የማብቃት ስራ መሆኑን አንስተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጭነት የተጀመረው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የዓለምን ምርጥ ተሞክሮዎች በመውሰድ በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ መተግበሩን ጠቁመዋል። ዓላማውም በከተሞች አገልግሎትን በአንድ ቦታ መስጠት እና የተገልጋዮችን እርካታ ማረጋገጥ መሆኑን ተናግረዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ለከተሞች አገልግሎት አሰጣጥ መዘመን ትልቅ እገዛን የሚያደርግ መሆኑን ጠቁመዋል።   ስርዓቱ አካታች ለሁሉም ዜጋ ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሆኑን ገልጸው፤ የመሶብ ዋና ማእከል በዚህ ዓመት ግንባታው እንደሚጀመር ተናግረዋል። እስካሁን 21 የመሶብ ማእከላት ወደ ስራ መግባታቸውን ገልጸው፤ በዚህ ዓመት 70 ተጨማሪ ማእከላት ተመርቀው ወደ ስራ እንደሚገቡ አመላክተዋል። የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እንደ ሀገር የበለጸገች ሀገር የመገንባት ጥረቶች አንዱ አካል መሆኑን በመግለጽ፤ ለአገልግሎቱ የሚያስፈልጉ መሰረተ ልማቶችን ቅድሚያ ሰጥቶ መስራት እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት ያስገኛል-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Nov 16, 2025 110
አዲስ አበባ፤ሕዳር 7/2018 (ኢዜአ)፡- ብልሹ አገልግሎት አሰጣጥን በማስወገድ ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት በመስጠት ረገድ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሚና የጎላ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የደሴ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።   በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር በተለያዩ መድረኮች ሕዝቡ ካነሳቸው ጉዳዮች አንዱ የአገልግሎት አሰጣጣችሁን ፈትሹ፤ ከእጅ መንሻ ነጻ የሆነ አገልግሎት ልናገኝ ይገባል የሚል ነበር ሲሉ አውስተዋል። በዚህም መሠረት በተቋማት የሚስተዋሉ ብልሹ አገልግሎት አሰጣጦችን በማስወገድ ዘመኑን የዋጀና ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ወደ ሥራ እያስገባን ነው ብለዋል። አስተዋዩ የደሴ ሕዝብ ልማት ፈላጊ፣ ለፍትሕ የቆመ፣ በውይይት የሚያምን፣ በኢትዮጵያዊነቱ የሚኮራና የጸና መሆኑንም በንግግራቸው አንስተዋል። ደሴ ከተማ በከፍተኛ የልማት እንቅስቃሴ ውስጥ እንደምትገኝ ተመልክተናል ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህን የልማት ጉዞ በማሳለጥ ረገድ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት የጎላ ሚና እንዳለው አስገንዝበዋል።   መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በተለያዩ ተቋማት የሚሰጡ አገልግሎቶችን ወደ አንድ ማዕከል በማምጣት፣ ከዚህ በፊት በማንዋል ይሰጥ የነበረውን የመንግሥት አገልግሎት በዲጂታል ፈጣን አገልግሎት በመስጠት የተገልጋዩን እንግልት የሚቀንስ መሆኑንም አስረድተዋል። ተገልጋዮች ጊዜያቸውን፣ ገንዘባቸው ብሎም ጉልበታቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ በማድረግ ረገድ መሶብ የአንድ ማዕከል ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለውም ገልጸዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከሲቪል ሰርቪስ ማሻሻ ሪፎርሞች ውስጥ አንዱ አካል እንደሆነ ገልጸው፤ በሕዝብና በመንግሥት መካከል ያለውን ጥብቅ ቁርኝት ወደ ተሻለ ደረጃ የሚያሳድግ መሆኑን ጠቅሰዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን በይበልጥ ማስፋፋትና ማጠናከር እንደሚገባም አሳስበዋል።   በሌላ በኩል የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ወደ ሁሉም አካባቢዎች መድረስ እንዳለባቸው ተናግረዋል። ጽዳትና ውበት የደሴ መገለጫዎች ሊሆኑ እንደሚገባ ጠቁመው፤ ለዚህ ደግሞ የከተማዋ ነዋሪዎች በተለይም የንግዱ ማኅበረሰብ ግብሩን በወቅቱና በታማኝነት መክፈልና ተጨማሪ አስተዋጽኦም በግሉ ማበርከት እንደሚጠበቅበት አመላክተዋል። የኮሪደር ልማትና የኢትዮጵያን ብልጽግና በሚፈለገው ልክ ለማሳካት እያንዳንዱ ማኅበረሰብ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል። ሰላምና ልማት ተመጋጋቢ በመሆናቸው ሕዝቡ ሰላሙን ማስጠበቅ እንዳለበትም በንግግራቸው አጽንኦት ሰጥተዋል።
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ህዝቡ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያለውን ቅሬታ በዘላቂነት ይፈታል
Nov 15, 2025 113
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ህዝቡ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያለውን ቅሬታ በዘላቂነት እንደሚፈታ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የደሴ ከተማን መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት አስጀምረዋል፡ ፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚህ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ደሴ ከተማ በሀገረ መንግሥት ግንባታ ዘመን ተሻጋሪ ገድል የጻፈች፣ የሰለጠነ ማህበረሰብ የገነባች፣ የዘመናዊ መገለጫ ከተማ መሆኗን ገልጸዋል፡፡ ህዝቡ አስተዋይ፣ ለፍትህ የቆመ፣ በውይይት የሚያምን፣ የሰላም አምባሳደር የልማት አርበኛ በኢትዮጵያዊነቱ የማይደራደር መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የወሎ ምድር ለኢትዮጵያዊነት የመደመር ቅኝት ማሳያ፣ ድንቅ እሴት እንደ ቦርከና ወንዝ ሞልቶ የሚፈስበት የአብሮነት እና የመዋደድ ተምሳሌት መሆኑንም አንስተዋል፡፡ ወሎ የጥበብ መፍለቂያና የዕውቀት ማዕድ መሆኗን የገለጹት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የወሎዋ ዕምብርት ደሴ ከተማ አሁን በከፍተኛ የልማተ እንቅስቃሴ ላይ ትገኛለች ብለዋል፡፡ የደሴ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት በከተማዋ የተጀመረውን የልማት ጉዞ ለማሳለጥ የጎላ አበርክቶ እንደሚኖረው ገልጸዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢኒሼቲቭ የሆነው መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት በተለያዩ አካባቢዎች በማንዋል ሲሰጥ የቆየውን የመንግሥት አገልግሎት በአንድ ማዕከል ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡ በመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት የተገልጋዮችን ጊዜና ጉልበት በመቆጠብ በህዝብና መንግሥት መካከል ያለውን ጥብቅ ቁርኝት ወደ ተሻለ ደረጃ እንደሚያሳድግ ገልጸዋል፡፡ ብልሹ አሰራርን በማስወገድ ዘመኑን የዋጀና ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል ገልጸው፤ በደሴ ከተማ የተሰራው ማዕከል የህዝቡን የረጅም ጊዜ የፈጣን አገልግሎት ጥያቄ ምላሽ የሚሰጥ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በለውጡ መንግሥት ደሴ የብልፅግና ብርሃን ወጋገን ፈንጥቃለች፣ ለኗሪዎቿ ምቹ የበለፀገች እና የተዋበች ከተማ መሆን የሚያስችላትን የተስፋ ጎዳና ጀምራለች ብለዋል፡፡ የመጀመሪያው ምዕራፍ የደሴ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ውበት እየገለጠ መሆኑን በመጥቀስ፤ ለተሻለ አፈጻጸም ህዝቡና አመራሩ ተጋግዞ መስራት እንዳለበት አሳስበዋል፡፡ ሰላምና ልማት ተመጋጋቢ መሆናቸውን የገለጹት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የተጀመረው ልማት ከግብ እንዲደርስ ህዝቡ የሰላም ዘብነቱን አጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም