ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ኢኒስቲትዩቱ ይፋ ያደረገው የእንሰት መፋቂያ ቴክኖሎጂ የሥራ ጫናን ከማቅለል ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጥሯል
Jan 24, 2026 62
ሀዋሳ፤ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፦የባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ከአርባ ምንጭ ዩኒቨርስቲ ጋር በመቀናጀት ይፋ ያደረገው የእንሰት መፋቂያ ቴክኖሎጂ የሥራ ጫናን ከማቃለል ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሀብት ልማት፣ሥራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። የቋሚ ኮሚቴው አባላት በሲዳማ ክልል ደቡባዊ ሲዳማ ዞን አለታ ወንዶ ወረዳ በኢንስቲትዩቱ የተሰራ ዘመናዊ የእንሰት መፋቂያ ቴክኖሎጂ ሽግግር ስራን ተመልክተዋል። የቋሚ ኮሚቴው ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሺ ሀሰን በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፣ኢንስቲትዩቱ የህብረተሰቡን ኑሮ የሚያቃልሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እያፈለቀ ይገኛል። ከእነዚህ ውስጥ በሴቶች ላይ የሚደርሰውን የስራ ጫና የሚያቃልል የእንሰት መፋቂያ፣ መጭመቂያና መቁረጫ መሳሪያ አንዱ ነው ብለዋል። በርካታ ሴቶች በእንሰት ሥራ እንደሚሰማሩ ገልጸው፣ እንዲህ አይነት ቴክኖሎጂዎች መምጣታቸው የሥራ ጫናውን ከማቃለል ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል የሚፈጥር ነው ብለዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የኢትዮጵያ አየር ኃይል ፈጣን እድገት ለአፍሪካ ሀገራት አብነት ይሆናል - የአፍሪካ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች
Jan 23, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር ኃይል ፈጣን እድገት ለአፍሪካ ሀገራት አብነት ይሆናል ሲሉ የአፍሪካ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት ክብረ በዓልን በማስመልከት የተዘጋጀው የአቪዬሽን ኤክስፖ ተከፍቷል። ኤክስፖው የወደፊቱን የአቪዬሽን አቅም በጋራ እንገንባ በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ ሲሆን፤ ኤክስፖውን የጎበኙ የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎች፤ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ለአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ በሚሆን አግባብ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ ስለመሆኑ መታዘባቸውን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የቦትስዋና ኤምባሲ ወታደራዊ አታሼ ኮሎኔል ሞታሲ ቼሌኒያኔ፤ የኢትዮጵያ አየር ሃይል በአቪዬሽን፣ ኢንጂነሪንግና ቴክኖሎጂ ዘርፍ አስደማሚ ለውጥ ውስጥ መሆኑን ከኤክስፖው መመልከታቸውን ገልጸዋል። በተለይ አየር ኃይሉን ጥገናን ጨምሮ በሌሎች ቁልፍ የዘርፉ ምህንድስና ስራዎች ራሱን ለመቻል እያከናወነ ያለው ስራ የሚደነቅ መሆኑን አንስተው፤ በርካታ የአፍሪካ ሀገራት ከዚህ ልምድ መውሰድ እንዳለባቸው ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የናሚቢያ ኤምባሲ ወታደራዊ አታሼ ማካንዚ ቺቤራ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ ባለፉት ጊዜያትም ሆነ አሁን ላይ የኢትዮጵያ አየር ኃይል የራሱን እና የአፍሪካን አቅም ለማሳደግ ጥረት እያደረገ ነው። የአፍሪካ ሀገራት በጋራ እና በትብብር ከሰሩ ብዙ ርቀት መሄድ እንደሚችሉ ጠቁመው፤ በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ አየር ሃይል የወሰደውን ተነሳሽነት አድንቀዋል። በኢትዮጵያ የጋቦን ኤምባሲ ወታደራዊ አታሼ ኮሎኔል አርሲዴ አንጉሌ፤ የኢትዮጵያ አየር ሃይል ሀገር የሚወክል ተቋም እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል። ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ጥሩ ምሳሌ ነው ብለዋል።
የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ሥራችንን ለማዘመንና ለማቀላጠፍ አግዞናል -ሰልጣኞች
Jan 23, 2026 160
ወልቂጤ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮ-ኮደርስ ያገኙት ስልጠና የዲጂታል ክህሎታቸውን በማሳደግ ሥራቸውን ለማዘመንና ለማቀላጠፍ እንዳገዛቸው በወልቂጤ ከተማ የኮደርስ ሰልጣኞች ገለጹ። መንግስት ለዜጎች ያመቻቸው የአምስት ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና ዜጎች ከዲጂታል ዓለሙ ጋር ለመራመድ የሚያስችላቸውን የቴክኖሎጂ እውቀትና ክህሎት እያስጨበጣቸው ነው። በወልቂጤ ከተማ አስተዳደር በተለያዩ ተቋማት የሚሰሩ ሠራተኞችም ስልጠናውን እንዲወስዱ በአስተዳደሩ የተመቻቸላቸውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም የዲጂታል እውቀታቸውን እያሳደጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። ስልጠናውን የወሰዱት ሠራተኞች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በኢትዮ-ኮደርስ በተለያዩ ዘርፎች ያገኙት ስልጠና የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማሳደግ ሥራቸውን እንዲያዘምኑና ውጤታማ እንዲሆኑ እያገዛቸው ነው። በወልቂጤ ከተማ የኢንተርፕራይዝና ሥራ ዕድል ፈጠራ ጽህፈት ቤት ባለሙያ ወጣት ሰለሞን ደርብ በኢትዮ ኮደርስ በዳታ ፕሮግራሚንግ፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎትና በአንድሮይድ ዘርፎች ስልጠና ወስዶ ክህሎቱን ማሳደጉን ተናግሯል፡፡ በአሁኑ ወቅትም በሌሎች ዘርፎች ተጨማሪ ስልጠና እየወሰደ መሆኑን ጠቁሞ፣ በኮደርስ ስልጠና ባገኘው እውቀት በትርፍ ሰአቱ ተጨማሪ ሥራ ለመፍጠር እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ተናግሯል። የከተማው ሳይንስ እና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት ባለሙያ ወጣት ጅብሪል መጀል በበኩሉ፤ የዲጂታል እውቀቱን ለማሳደግ የሚያግዘውን የኮደርስ ስልጠና በመውሰድ ከራሱ ባለፈ ሌሎችን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ተናግሯል። ያገኘው ስልጠና በኮምፒውተር ሳይንስ በዲግሪ ለመማር መነሳሳት እንደፈጠረለት ገልጾ፣ በቀጣይም በተለያዩ ዘርፎች የሚሰጠውን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዱን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጿል። በማይክሮ ሶፍት መተግበሪያዎች በወሰደው ስልጠና ያገኘውን እውቀትና ክህሎት በተቋም ሥራ በመተግበር ሥራውን ለማቀላጠፍና ለችግር መፍቻነት እየተጠቀመበት መሆኑን ተናግሯል። በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዲጂታል ቴክኖሎጂ ያለንን እውቀትና ክህሎት በማሳደግ ከዲጂታል ዓለም ፈጣን እድገት ጋር ለመጓዝ የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ ሌላኛዋ ሰልጣኝ ወይዘሮ አቻምየለሽ ዘርጋ ናቸው። ስልጠናው ከኋላቀር የመረጃ አያያዝ ስርዓት በማላቀቅ የግልና የመስሪያ ቤት መረጃዎችን ለማዘመን የሚያስችል እውቀት እንዳገኙበት ተናግረዋል፡፡ በኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና በአራት የተለያዩ ዘርፎች የቀሰሙት እውቀት በቴክኖሎጂ ብቁና ተወዳዳሪ ባለሙያ እንዳደረጋቸው የተናገሩት ደግሞ የከተማው ንግድና ገበያ ልማት ባለሙያ አቶ ጅላሉ ሙዘይን ናቸው ። ስልጠናው የተለያዩ አገልግሎት የሚሠጡ ሶፍትዌሮችን አበልጽገው እንዲጠቀሙ እድል መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡ የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሃምዱ ካሚል፤ በከተማው እስካሁን ድረስ 20ሺህ የሚጠጉ ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስደው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። በቀጣይ ስልጠናውን በሁሉም የመንግስት መዋቅር ተደራሽ በማድረግ ዜጎች የቴክኖሎጂ ክህሎትና ዕውቀታቸውን ለማሳደግ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።
ኮሌጆች ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት የማይተካ ድርሻ አላቸው
Jan 23, 2026 81
ቦንጋ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት በሚደረገው ርብርብ ብቃት ያለው የሰው ሀይል በማፍራት የማይተካ ድርሻ እንዳላቸው የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በቦንጋ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ኢትዮ ኮደርስ ስልጠናና ፋይዳ መታወቂያን ተደራሽ ለማድረግ ያለመ የንቅናቄ መድረክ አካሂዷል። በመድረኩ የተገኙት የቢሮ ምክትል ሀላፊና የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ዘርፍ ሀላፊ አቶ ምትኩ አስፋው እንደገለጹት፤ ኮሌጆች ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት በሚደረገው ርብርብ ብቃት ያለው የሰው ሀይል በማፍራት የማይተካ ሚና አላቸው፡፡ ለዚህም ራሳቸውን በቴክኖሎጂ ግብአቶች በማደራጀት ለሰው ሀይል ልማት ትኩረት መስጠት እንዳለባቸው አክለዋል። ለዲጂታል ኢትዮጵያ መሳካት ድርሻ ላላቸው የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እና ለፋይዳ መታወቂያ ኢንሼቲቮች ትኩረት መስጠት ሌላው ተግባራቸው መሆን እንዳለበትም አስገንዝበዋል። በክልሉ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዓመት ከ110 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ እስካሁን ድረስ 28 ሺህ 90 ሰዎች እንደወሰዱና 8 ሺህ የሚጠጉትም ሰርተፊኬት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ዜጎችን የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ ከማድረግ አንጻር በዓመቱ ለማሳካት ከታቀደው ውስጥ እስካሁን ድረስ 246 ሺህ 436 ዜጎችን የመታወቂያው ባለቤት ለማድረግ መቻሉንም ጠቁመዋል። ሥራውን ለማሳካትም የአሁኑ የንቅናቄ መድረክ ተደማሪ አቅም ይሆናል ብለዋል። በመድረኩ የተገኙት የካፋ ዞን ኢንዱስትሪና ኢኖቬሽን መምሪያ ሀላፊ አቶ ተፈሪ ታደሰ በበኩላቸው፤ በዞኑ በኮደርስ ስልጠና በፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ሥራዎች እንደተጀመሩና ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። ኢንሼቲቮቹን ለማሳካት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ከሁለተኛ እና አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ጋር በቅንጅት እንዲሰሩ መደረጉንም ጠቁመዋል።
የአቪዬሽን ኤክስፖው የኢትዮጵያ የአፍሪካ አቪዬሽን ማዕከልነት ሚናን የሚያጠናክር ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jan 23, 2026 101
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የአቪዬሽን ኤክስፖው የኢትዮጵያ የአፍሪካ አቪዬሽን ማዕከልነት ሚናን እንደሚያጠናክር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ዛሬ የኢፌዲሪ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት ክብረ በዓልን በማስመልከት በተሰናዳው የአቪዬሽን ኤክስፖ 2026 መክፈቻ ላይ መገኘታቸውን ጠቁመዋል። የአቪዬሽን ኤክስፖው “ወደፊት መብረር፣ የጋራ ነገን መገንባት” በሚል መሪ ቃል መዘጋጀቱን አመልክተዋል። ኤክስፖው የአቪዬሽን ቴክኖሎጂን፣ ክህሎትን፣ ትብብርን የማሳደግና በማደግ ላይ ያለውን የኢትዮጵያ የአፍሪካ አቪዬሽን ማዕከልነት ሚናን ለማጠናከር የሐገር ውስጥ እና የውጭ ተባባሪ አካላትን በአንድ መድረክ ያገናኘ መሆኑን ተናግረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢፌዲሪ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት በማስመልከት በተዘጋጀው የአቪዬሽን ኤክስፖ መክፈቻ ላይ ተገኝተዋል
Jan 23, 2026 86
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው የኢፌዲሪ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት ክብረ በዓልን ምክንያት በማድረግ በተሰናዳው የአቪዬሽን ኤክስፖ 2026 ይፋዊ የመክፈቻ መርሃ ግብር ላይ ተገኝተዋል። ኤክስፖው “የወደፊቱን የአቬሽን አቅም በጋራ እንገባ” በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። ኤክስፖው ኢትዮጵያ ለአቪዬሽን እና ኤሮስፔስ ልማት፣ አለም አቀፍ ትብብርን በማጠናከር እና ሀገራችንን በአቪዬሽን ልማት የቀጣናው እና አኅጉሩ የፈጠራ፣ የክህሎት ልማት እና የዘላቂ እድገት ማዕከል ማድረግ ላይ ያላትን ጽኑ አቋም እና ተግባር የሚያሳይ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አመልክቷል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የትምህርት ጥራትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ አጋዥ ሚና ይኖረዋል
Jan 23, 2026 76
አክሱም ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትግበራ የትምህርት ጥራትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ አጋዥ ሚና እንደሚኖረው የአክሱም ከተማ መምህራን ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ ቀጣይ 5 ዓመታት የዲጂታል ጉዞ የሚመራበትን ''ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ'' በቅርቡ ይፋ ማድረጋቸው ይታወሳል። ዲጂታል ቴክኖሎጂ የሰውን ልጅ የመፈጸም አቅም በማሳደግና የሀገርን ልማት በማሳለጥ ረገድ ቁልፍ ሚና ይጫወታል። በኢትዮጵያ የትምህርት ጥራት ሥብራትን ለመጠገን እየተደረገ ያለውን ጥረት ውጤታማ ለማድረግ የቴክኖሎጂ ተደረሽነትን ማስፋት ቁልፍ ጉዳይ ነው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአክሱም ከተማ መምህራንም በዚህ ሀሳብ ይስማማሉ። በአክሱም የአልሙናይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህር ያሬድ መኮንን፣ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥና ተማሪዎችን በቂ ዕውቀት ለማስጨበጥ ከፍተኛ እገዛ ያደርጋል ብለዋል። የፈተና አሰጣጡ በዲጂታል ቴክኖሎጂ መታገዙም ኩረጃን የሚያስቀርና የፈተና ደህንነትን የሚያስጠብቅ መሆኑንም ነው ያመለከቱት። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትግበራ የትምህርት ጥራትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ አጋዥ ሚና እንደሚኖረው በመግለጽ። መምህር ሙዑዝ በየነ በበኩላቸው፣ የዲጂታል 2030 ስትራቴጂ ትግበራ ተማሪዎች ተግባር ተኮር ዕውቀትና ክህሎት እንዲያዳብሩ ያግዛል ብለዋል። የመማር ማስተማር ሂደቱን ፈጣንና ቀልጣፋ ከማድረግ ባለፈ የትምህርት ተደራሽነትን ለማስፋት ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ ስትራቴጂው ተማሪዎች አጋዥ መጽሐፍትን በቀላሉ እንዲያገኙና የዕውቀት አድማሳቸውን እንዲያሰፉ ቁልፍ ሚና ይጫወታል ያሉት ደግሞ መምህር ግደይ ካሓሱ ናቸው። በትምህርት ጥራት ላይ ይነሳ የነበረውን ተደጋጋሚ ቅሬታ ለመፍታትም ከፈተና አወጣጥ ጀምሮ ያለውን ሂደት ግልጽና ተጠያቂነት የሰፈነበት እንዲሆን ያግዛል ነው ያሉት።
ባዮ ጋዝ በመጠቀማችን ጤንነታችንን መጠበቅ ችለናል- አርሶ አደሮች
Jan 23, 2026 70
ጎንደር ፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ)፡- ባዮ ጋዝ መጠቀም በመቻላቸው ከሚያገኙት ጥቅም በሻገር ጤንነታቸውን ለመጠበቅ እንዳገዛቸው የማእከላዊ ጎንደር ዞን አርሶ አደሮች ተናገሩ፡ በዞኑ ዘንድሮው ዓመት 180 የባዮ ጋዝ ማብላያዎች የግንባታ ስራ እየተከናወነ መሆኑ ተመልክቷል። በማእከላዊ ጎንደር ዞን የምእራብ በለሳ ወረዳ ነዋሪ አቶ መኳንንት የአብስራ ለኢዜአ እንደገለጹት፤የባዮ ጋዝ ማብላያ በመገንባት ላለፉት ሶስት ዓመታት ለምግብ ማብሰልና ለመብራት እየተጠቀሙ ይገኛሉ። ይህም ቀደም ሲል ለምግብ ማብሰያና ለመብራት አገልግሎት ማገዶን በመጠቀም ጭሱ በጤናቸው ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ለመቀነስና ለሀይል አቅርቦት ይጨፈጭፍ የነበረን ደን ለመጠበቅ እንደቻሉ ገልጸዋል። የባዮ ጋዙ ለኃይል አቅርቦት ከመዋሉም ባሻገር ተረፈ ምርቱን ለመሬታቸው የተፈጥሮ ማዳበሪያ በመጠቀም ምርታማነታቸውን ማሳደግ መቻላቸውን የገለጹት ደግሞ የወገራ ወረዳ ነዋሪ አርሶአደር በላይ ቸርነት ናቸው፡፡ የባዮ ጋዝ ሃይል አቅርቦቱ ለአጠቃቀም ቀላልና ልጆቻቸው ትምህርታቸውን በማታ ለማጥናት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል።፡ በጎንደር ዙሪያ ወረዳ የምንዝሮ ቀበሌ ነዋሪ አርሶአደር ተሾመ ንጉሴ በበኩላቸው የባዮ ጋዝ ቴክኖሎጂ ሴቶችና ህጻናትን ማገዶ ፍለጋ ይደርስባቸውን የነበረውን መንከራተት ያስቀረ ነው ብለዋል፡፡ በማእከላዊ ጎንደር ውሃና ኢነርጂ መምሪያ የፕላንና ፕሮግራም ቡድን መሪ አቶ ማሩ ታደሰ እንደገለጹት፤ በዘንድሮ ዓመት በ13 ወረዳዎች 180 የባዮ ጋዝ ማብለያዎች ግንባታ ለማከናወን እየተሰራ ነው። እስካሁንም ተጠቃሚ አርሶ አደሮችን መለየት፣ የኢንዱስትሪ ውጤቶችን የማቅረብና አርሶ አደሩ እንደ አሸዋና ድንጋይ ያሉ የአካባቢ ቁሳቁሶችን እንዲያቀርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። የባዮ ጋዝ ማብለያዎቹን ግንባታ በዚህ ዓመት መጨረሻ ሙሉ በሙሉ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት በማብቃት አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
በዩኒቨርሲቲው የተለያዩ ጥናታዊ ጽሁፎችን ጨምሮ ከ400ሺህ በላይ መጽሐፍት በዲጂታል ሥርዓት ተደራጅተዋል
Jan 23, 2026 66
ጎንደር፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎችን ጨምሮ ከ400ሺህ በላይ መጽሐፍት በዲጂታል ሥርዓት መደራጀታቸውን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት አሥራት አፀደወይን(ዶ/ር) ገለጹ። ጎንደር ዩኒቨርሲቲ በየዓመቱ የሚያዘጋጀው የመጽሐፍት ዐውደ ርዕይ ''መጽሐፍት ለንባብ፣ ንባብ ለዕውቀት፣ ዕውቀት ለህይወት'' በሚል መሪ ሃሳብ ትናንት ተጀምሯል። የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት አሥራት አፀደወይን(ዶ/ር) በዐውደ ርዕዩ መክፈቻ ባደረጉት ንግግር የወጣቱን የንባብ ባህል ለማሳደግ አዳዲስ አሰራሮች ተግባራዊ እየተደረጉ ነው ብለዋል። ዲጂታል ቤተ-መጽሐፍትን ማስፋፋትና መጽሐፍትን ዲጂታላይዝድ ማድረግ ንባብን ለማበረታታትና አንባቢ ትውልድ ለመፍጠር ወሳኝ ሚና አለው ብለዋል። ከዚህ አኳያ ዩኒቨርሲቲው የዲጂታል ቤተ-መጽሐፍት በማቋቋምና ጥናታዊ ጽሁፎችና የተለያዩ መጽሐፍትን በዲጂታል ሥርዓት በማደራጀት አንባቢ ትውልድ አንዲፈጠር የድርሻውን እየተወጣ ነው ብለዋል። እስካሁንም ከ400ሺህ በላይ የታሪክ፣ የሳይንስና የምርምር መጽሐፍትን ጨምሮ ከ10ሺህ በላይ የጥናት ውጤቶችን ወደ ዲጂታል በመቀየር ለተማሪዎች በቀላሉ ተደራሽ ማድረግ መቻሉን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ደራሲያን ማሕበር ፕሬዝዳንት የዝና ወርቁ በበኩላቸው፣ በኢትዮጵያ የንባብ ባህልን ለማሳደግ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሚና የጎላ ነው ብለዋል። ተቋማቱ ወጣቱ መጽሐፍትን በቀላሉ ማግኘት የሚችልባቸው ዲጂታል አሰራሮች ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባቸውም አንስተዋል። ለአንድ ሳምንት በሚቆየው የመጽሐፍት ዐውደ ርዕይ የዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ ደራሲያን፣ አሳታሚዎችና መጽሐፍት አከፋፋዮች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከዲጂታል ዓለም ጋር ለመተዋወቅ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Jan 22, 2026 131
ወላይታ ሶዶ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከዲጂታል ዓለም ጋር ይበልጥ ለመተዋወቅና በዘርፉ የራሳቸውን ሥራ ፈጥረው ለመንቀሳቀስ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው የወላይታ ሶዶ ከተማ ሰልጣኞች ተናገሩ። መንግስት በመላው ኢትዮጵያ ለአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን የኮደርስ ስልጠና ለመስጠት ግብ ጥሎ እየሰራ ነው። በወላይታ ሶዶ ከተማም 18 ሺህ 400 ዜጎችን በኢትዮ ኮደርስ ለማሰልጠን እየተሰራ ይገኛል። የኮደርስ ስልጠና የወሰዱ የከተማዋ ነዋሪዎች ስልጠናው ከዲጂታል ዓለም ጋር ይበልጥ እንዲተዋወቁና የራሳቸውን ሥራ በመፍጠር ተጠቃሚ ለመሆን ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት ሰልጣኞች መካከል አቶ ደምሴ አሻ፤ በኮደርስ በተለያዩ ዘርፎች የወሰዷቸው ስልጠናዎች የቴክኖሎጂ እውቀታቸውን በማሳደግ በዲጂታል ዓለም እኩል ለመንቀሳቀስ የሚያስችል ክህሎት እንዳስጨበጧቸው ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም ባገኙት እውቀት የራሳቸውን ሥራ ፈጥረው እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ገልጸው፣ በተጨማሪም በተለያዩ ተቋማት ያሉ ሠራተኞችን በማሰልጠን ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መምጣታቸውን ተናግረዋል። ስልጠናው በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ ያለኝን እውቀት አሳድጎልኛል ያሉት ደግሞ ሒሩት አርጃ ናቸው። በኢትዮ ኮደርስ የፕሮግራሚንግ ስልጠና መውሰዳቸውንና በአሁኑ ወቅት በሰውሰራሽ አስተውሎት ስልጠናቸውን እየተከታተሉ መሆናቸውን ገልጸው፣ ከስልጠናው ዲጂታል ዓለምን የሚመጥን እውቀት መቅሰማቸውን ተናግረዋል። ስልጠናው የኮምፒውተርና የዲጂታል እውቀቴን በማሳደግ ከዓለም ጋር ይበልጥ የምቀራረብበትን ዕድል ሰጥቶኛል ያሉት ደግሞ አቶ ሙሉጌታ ዶላ ናቸው። በስልጠናው ያገኙት እውቀት በዲጂታል ዓለም ተወዳዳሪ እንደሚያደርጋቸው ተናግረው፣ ያገኙት እውቀት ከተቋማዊ አሰራር ጋር በማስተሳሰር ውጤታማ ሥራ ለማከናወን እንዳስቻላቸውም ገልጸዋል። የወላይታ ሶዶ ከተማ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ ተሻለ ታደሰ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ መምሪያው ስልጠናውን ተደራሽ በማድረግ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተጀመረውን ሥራ ለማገዝ እየሰራ ነው። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከተጀመረ ወዲህ በከተማው ከ10 ሺህ በላይ ሰዎች ስልጠናቸውን አጠናቅቀው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን ገልጸው፣ ከነዚህ ውስጥ 3ሺህ 480 የሚሆኑት ባለፉት ስድስት ወራት ስልጠናውን የወሰዱ ናቸው ብለዋል። በተያዘው ዓመት ዕቅዱን ለማሳካትም የአንድ ጀንበር ምዝገባ ንቅናቄ በማካሄድና በሁሉም አካባቢዎች ያሉ ዜጎችን ለማሰልጠን በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ስልጠናው በዲጂታል ክህሎት የዳበረ ማህበረሰብ ለመፍጠርና የዲጂታል ዓለምን በፍጥነት የሚላመድ ትውልድ ለማፍራት የጎላ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል።
በአፋር ክልል 2 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዓመት ዕድሜ ያለው "ፓራንትሮፐስ" የተሰኘ የሰው ዘር ቅሪተ አካል ተገኘ
Jan 21, 2026 206
አዲስ አበባ፤ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ አፋር ክልል ሚሌ-ሎጊያ ፓሊዮአንትሮፖሎጂ መካነ ቅርስ ስፍራ 2 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዓመት ዕድሜ ያለው "ፓራንትሮፐስ" የተሰኘ የሰው ዘር ቅሪተ አካል መገኘቱ ተገለጸ። በአፋር ክልል ሚሌ-ሎጊያ የፓሊዮአንትሮፖሎጂ መካነ ቅርስ ስፍራ የተገኘው ቅሬተ አካሉም ከዚህ ቀደም ተገኝቶ የማያውቅ የቅድመ ሰው ዘር መሆኑ ተመላክቷል። የቅድመ ሰው ዘር ቅሪተ አካሉን ለማግኘት በአሜሪካ ቺካጎ ዩኒቨርስቲ የዘርፉ ተመራማሪ ፕሮፌሰር ዘረሰናይ ዓለምሰገድ የተመራ ቡድን ከፍተኛ እንቅስቃሴ አድርጓል። የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኤሊያስ ሽኩር፤ የሀገር ውስጥና የውጭ ተመራማሪዎች የምርምር ውጤቶች የኢትዮጵያን የሰው ዘር መገኛነት የሚያጠናክሩ ናቸው ብለዋል። በኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የበርካታ ቅድመ ሰው ዝርያ ቅሪተ አካል ግኝቶችም የዓለምን ማህበረሰብና ተመራማሪዎችን ቀልብ እየሳበ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የፕሮፌሰር ዘረሰናይ ዓለምሰገድ የጥናት ቡድን በአፋር ክልል ያገኘው ፓራንትሮፐስ የተሰኘ የቅድመ ሰው ዘር ቅሪተ አካልም የኢትዮጵያን የሰው ዘር መገኛነት ዳግም ያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የቅድመ የሰው ዘር መገኛነት የጥናት ውጤት ማረጋገጫዎችም በቱሪዝም ዘርፍና በዲፕሎማሲ እንቅስቃሴ ጉልህ ሚና እንደሚጫወት አንስተዋል። ኢትዮጵያ ለቅድመ ሰው ዘር ቅሪት አካል ፍለጋና ለሰው ዘር አመጣጥ ጥናት ያላትን ልዩ ጠቀሜታ አጉልቶ እንደሚያሳይ አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ወጣት ተመራማሪዎች በዘርፉ የሚኖራቸውን የላቀ የጥናትና ምርምር ሚና ለማሳደግም ምቹ ሁኔታ የመፍጠር ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል። ለዚህም ብቃት ያላቸው የኢትዮጵያ አንትሮፖሎጂ ተመራማሪዎችን ለማፍራት ከውጭ የዘርፉ ሙያተኞች ጋር በቅርበት እንደሚሰራም ጠቁመዋል። የጥናት ቡድኑ መሪ ፕሮፌሰር ዘረሰናይ ዓለምሰገድ በበኩላቸው፤ ፓራንትሮፐስ የቅድመ ሰው ዘር ከ2 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዓመታት በፊት የኖረ የነበረ የሰው ዝርያ መሆኑን የጥናት ውጤቶቹ እንደሚያሳዩ አረጋግጠዋል። የቅድመ ሰው ዝርያው የተሻለ አካባቢን የመላመድ ባህሪ ያለው በመሆኑ በርካታ አካባቢዎች ላይ መኖሩን የሚያሳዩ የጥናት ውጤቶች እንደተገኙም አስታውቀዋል።
በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የተያዙ ግቦችን እውን ለማድረግ ለሰው ኃይል ልማት ትኩረት ተሰጥቷል
Jan 21, 2026 101
ሀዋሳ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦የብልጽግና ፓርቲ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የተያዙ ግቦችን እውን ለማድረግ የሰው ኃይል ልማት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አስታወቀ። ለብልጽግና ፓርቲ ዋናና ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት አመራሮችና ባለሙያዎች በተቀናጀ የተቋም ሀብት አስተዳደር ትግበራ ላይ ያተኮረ ስልጠና መስጠት ተጀምሯል። በሥልጠናው መክፈቻ ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል ሥራ፣ ክህሎትና ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክር ቤት አባል ሀገረፅዮን አበበ እንደገለጹት፣ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የተያዙ ግቦች እንዲሳኩ በፓርቲው ለሰው ኃይል ግንባት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በቴክኖሎጂ የተደገፈ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት፣ ምቹ የአሰራር ሥርዓቶችን በመዘርጋትና የሰው ኃይሉን በማብቃት ረገድ ውጤታማ ሥራ መሰራቱንም አስታውሰዋል። በተጨማሪም አሰራሮችን በቴክኖሎጂ በማዘመን ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት የተያዘው ግብ እንዲሳካም ፓርቲው ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተ መሆኑን ነው የገለጹት። ሥልጠናው በየደረጃው ባሉ የፓርቲው መዋቅሮች ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል መሆኑንም ጠቁመዋል። በብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የስትራቴጂክ ሥራ አመራርና ኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ ዋና ባለሙያ ጌትነት ሙላት በበኩላቸው፣ ስልጠናው በየደረጃው ያሉ የፓርቲው መዋቅሮች ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ወጥ የአሰራር ሥርዓትን እንዲዘረጉ ያግዛል ብለዋል። በየመዋቅሩ የሰው ኃይል፣ የግዥና ንብረት እንዲሁም የፋይናንስ አስተዳደርና ሌሎች ቁልፍ ተግባራትን በቴክኖሎጂ ታግዞ መስራት ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት የሚደረገውን ጥረት እንደሚያግዝ አንስተዋል። ፓርቲው ለሰው ኃይልና ጠንካራ ተቋም ግንባታ የሰጠውን ትኩረት መሠረት በማድረግ በክልሉ ሰፋፊ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በፓርቲው የሲዳማ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ስትራቴጂክ ሥራ አመራርና ኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ዘርፍ ኃላፊ ታምሩ ዩቴ ናቸው። ሥልጠናው ተቋማትን በማዘመንና የሰው ኃይልን በማብቃት ወጥና ቀልጣፋ ዲጂታል ሥርዓት ለመገንባት ምቹ አጋጣሚ ይፈጥራል ብለዋል። ዛሬን ጨምሮ ለአራት ቀናት በሚቆየው ስልጠና ከፓርቲው ዋናና ከቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች የተውጣጡ አመራሮችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡
የኮደርስ ስልጠና በዘርፉ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ነው
Jan 21, 2026 104
ዲላ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦ የኮደርስ ስልጠና ጥልቅ እውቀት በማስጨበጥ በዘርፉ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል ነው ሲሉ የኮደርስ ሰልጣኞች ተናገሩ። በጌዴኦ ዞንና ዲላ ከተማ የስልጠናው ተሳታፊዎችና አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ባለሙያዎች፤የኮደርስ ስልጠና ጥልቅ እውቀት በማስጨበጥ በዘርፉ በዓለም ደረጃ ተወዳዳሪ ለመሆን የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የስልጠና ዕድሉ ማንም ሊያመልጠው አይገባም ያሉት ሰልጣኞቹ፣ ስልጠናው ያላቸውን የቴክኖሎጂ እውቀት ከማሳደግ ባለፈ ስራቸውን በውጤታማነት ለማከናወን ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። በዞኑ የፋይናንስና ፕላን ልማት መምሪያ ባለሙያ አቶ ዳዊት ተፈራ፤ ከዚህ ቀደም በኢትዮ ኮደርስ በዳታ ፕሮግራሚንግ፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎትና በአንድሮይድ ዘርፎች የወሰዱት ስልጠና በዘርፉ የነበራቸውን ክህሎት እንዳሳደገው ተናግረዋል፡፡ በተለይ የዳታ ፕሮግራሚንግ ስልጠና ከተሰማሩበት የሥራ መስክ ጋር በእጅጉ የተቆራኘ በመሆኑ የመፈጸም አቅማቸውን እንዳሻሻለው ነው የገለጹት። በአሁኑ ወቅትም በፕሮግራሚንግ ዘርፍ ተጨማሪ ስልጠና እየወሰዱ መሆኑን ጠቁመው፣ ይህም እውቀታቸውን በማስፋት ተወዳዳሪነታቸውን እንደሚያሳድገው ተናግረዋል። ከዲጂታል ዓለም ፈጣን እድገት ጋር አብሮ ለመጓዝ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰድ ጠቀሜታ አለው ያሉት የዞኑ ሥራና ክህሎት መምሪያ ባለሙያ አቶ ሰለሞን አበበ ናቸው። ከዚህ ቀደም በዳታ ፕሮግራሚንግ ዘርፍ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸው በማይክሮ ሶፍት ሁሉም መተግበሪያዎች ላይ ያላቸውን ክህሎት አሳድጎላቸዋል። በተለይ መረጃ አያያዛቸውን በማዘመን ምቹ የሥራ አካባቢ መፍጠር መቻላቸውን ጠቅሰው በሌሎች ዘርፎችም አቅማቸውን ለማሳደግ የኮደርስ ስልጠና መጀመራቸውን ገልጸዋል። ስልጠናው ለቴክኖሎጂ ያለኝን ዝንባሌ ለማጎልበት መልካም አጋጣሚ ፈጥሮልኛል ያለችው ደግሞ የዲላ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ12 ክፍል ተማሪ መድሀኒት ተገኝ ናት። የጌዴኦ ዞን ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ ደረጀ ሾንጣ እንዳሉት፤ በዞኑ ከ16 ሺህ በላይ ዜጎች ስልጠናውን ተከታትለው በማጠናቀቅ የምስክር ወረቀት አግኝተዋል፡፡ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በዘርፉ ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋ ለማፍራት የሚደረገውን ጥረት እያገዘ መሆኑን ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅትም በ80 ማዕከላት በዘመቻ እየተሰጠ ባለው ስልጠናም ከ22 ሺህ በላይ ዜጎች እየተሳተፉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዲላ ከተማ እየተሰጠ ያለውን ስልጠና የመንግስት ሠራተኞችና አመራሮች፣ መምህራንና ተማሪዎች እየወሰዱ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የዲላ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ ፀሐይ ቦጋለ ናቸው። በዞኑና በዲላ ከተማ አስተዳደር በአንድ ጀንበር ንቅናቄ ከ34 ሺህ በላይ ዜጎች በ93 ማዕከላት የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እየወሰዱ መሆኑ ተመላክቷል።
ኢንስቲትዩቱ የመኖ እጥረትን ለመፍታት የጀመራቸውን የምርምር ሥራዎች የበለጠ ሊያጠናክር ይገባል
Jan 21, 2026 174
አዳማ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦ የባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የመኖ እጥረትን ለመፍታትና የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የጀመራቸውን የምርምር ሥራዎች የበለጠ ሊያጠናክር እንደሚገባ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሀብት፣ሥራ ሥምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። የቋሚ ኮሚቴው አመራሮችና አባላት በአዳማ ከተማ በሚገኘው የባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የምርምር ፕሮጀክቶች ላይ የመስክ ምልከታ አድርገዋል። በዚህ ጊዜ በምክር ቤቱ የሰው ሀብት ልማት፣ ሥራ ሥምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር)፤ ኢንስቲትዩቱ የህብረተሰቡን ችግር በተጨባጭ መፍታት የሚችሉ ምርምሮች ለማከናወን እያደረገ ያለውን ጥረት አድንቀዋል። ደረቅ ቆሻሻን ወደ እንስሳት መኖና የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለመለወጥ የሚያስችል የፈጠራ ቴክኖሎጂ እውን ማድረጉ የዚህ ማሳያ መሆኑን በመጥቀስ። በገጠርም ይሁን በከተማ በዶሮና ዓሳ እርባታ የተሰማሩ ወጣቶችና አርሶ አደሮች መኖን በቀላሉ በቤታቸው እንዲያዘጋጁ ድጋፍ በማድረግ የመኖ እጥረትን ለመፍታት የኢንስቲትዩቱ ሚና ወሳኝ መሆኑንም ነው ያብራሩት። ኢንስቲትዩቱ ጠቃሚ የምርምር ውጤቶችን በማስፋፋት በባዮ ኢኮኖሚ ዕድገት ውስጥ ሚናውን የበለጠ እንዲያጎላም ጠይቀዋል። መኖን በአገር ውስጥ ማምረት የውጭ ምንዛሬን በማስቀረት የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድግ መሆኑን ጠቅሰው፣ ኢንስቲትዩቱ በዚህ ረገድ የጀመራቸውን የምርምር ሥራዎች የበለጠ አጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል። የባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ተመራማሪ ፍሬው ታፈሰ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ኢንስቲትዩቱ ባለፉት ስምንት ወራት ቆሻሻን ወደ ከፍተኛ ፕሮቲን ያለው የእንስሳት መኖና የተፈጥሮ ማዳበሪያ የሚቀይር “ነብሳት” የተሰኘ ፕሮጀክት በመቅረፅ ውጤታማ ስራ ማከናወኑን ገልጸዋል። ቴክኖሎጂው ፍራፍሬን ጨምሮ የግብርናና የኢንዱስትሪ ተረፈ ምርቶችን በመፍጨትና በማብላላት ወደ መኖና የተፈጥሮ ማዳበሪያ የሚቀይር መሆኑን አስረድተዋል። አሁን ላይ በሳምንት 10 ኩንታል የዶሮ መኖ በማምረት በአዳማ ሰርቶ ማሳያና የስልጠና ጣቢያ የዶሮ እርባታ መጀመሩን ገልጸዋል። የዶሮ መኖን ከተረፈ ምርት የማግኘት፣ የማላመድና የማሳደግ ተግባራትን ወደ ተጠቃሚው ለማሸጋገር በሂደት ላይ መሆኑን አመልክተዋል።
ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ለፋይናንስ ተቋማት የደንበኞች አገልግሎትን ለማፋጠንና ደህንነቱን ለማስጠበቅ ትልቅ እገዛ ያደርጋል
Jan 21, 2026 93
ጭሮ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፡- ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የፋይናንስ ተቋማት ደንበኞችን መረጃ አያያዝ ለማዘመን፣ ፈጣንና ደህንነቱ የተጠበቀ አገልግሎት ለመስጠት ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ተገለጸ። ኢዜአ በጭሮ ከተማ ከሚገኙ የፋይናንስ ተቋማት የስራ ሀላፊዎች ጋር በፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት ላይ ቆይታ አድርጓል። የስራ ሀላፊዎቹ እንዳሉት ዲጂታል መታወቂያው የደንበኞች የዓይን፣ የፊት ገፅታና አሻራ በኤሌክትሮኒክስ መሳሪያ በመያዝ አንድ ሰው ወጥ መረጃን ለመያዝ ከማጭበርበር የፀዳ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል ነው። በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የጭሮ ኦዳ ቡልቱም ቅርንጫፍ ስራ አስኪያጅ አቶ በላይ የሗላሸት እንዳሉት የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በሐሰተኛ መታወቂያ የሚፈጸሙ የማጭበርበር ተግባራትን ለመከላከል ያስችላል። የዲጂታል መታወቂያ በኤሌክትሮኒክስ ዘዴ መረጃ መያዙ ተገልጋዩ አንድ ማንነት እንዲኖረው በማድረጉ ትክክለኛነቱን ለማረጋገጥ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ባንኩ አዲስ ለጀመረው የደንበኞች አገልግሎት አሰጣጠን የማሻሻል ስራን የሚያቀላጥፍ መሆኑንም ጠቁመዋል። በአዋሽ ባንክ የጭሮ ቅርንጫፍ የደንበኞች አገልግሎት እና ኦፕሬሽን ስራ አስከያጅ አቶ ቴዎድሮስ ሰለሞን በበኩላቸው የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ደንበኞችንና ባንኮች በተሟላ መልኩ እንዲተዋወቁ በማድረግ የአገልግሎት አሰጣጡን የሚያቀላጥፍ ነው። ደንበኛው በአንድ የፋይዳ ቁጥር ብቻ በመመዝገቡ ባንኮች የብድር አገልግሎት ሲሰጡ ደንበኞቻቸውን በሚገባ እንዲያውቁና የብድር ክትትሉን በተገቢው መልኩ እንዲያከናውኑ የሚያግዝ መሆኑን ተናግረዋል። የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ በፋይናንስ ተቋማት ውስጥ እየተተገበረ ያለውን ከወረቀት ነፃ አገልግሎት ለማቀላጠፍ የሚያግዝ ነውም ብለዋል። በኢትዮ ቴሌኮም የጭሮ ማዕከል ሽያጭ ባለሙያ አቶ ተንኮሉ በቀለ በበኩላቸው የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የአንድ ሰው መረጃን ወጥነት ባለው መንገድ በመመዝገብ ፈጣንና ዘመናዊ የአገልግሎት አሰጣጥ የሚያሰፍን መሆኑን ጠቁመዋል።
መተግበሪያው አገልግሎትን ለማቀላጠፍና ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን ለመከላከል ትልቅ ፋይዳ አለው
Jan 20, 2026 156
አዲስ አበባ፤ ጥር 12/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ይፋ ያደረገው መተግበሪያ ዳያስፖራው ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኝ ከማስቻሉም በላይ ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን ለመከላከል ትልቅ ፋይዳ እንዳለው የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ፍጹም አረጋ ገለጹ። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 'CBE Connect Digital Wallet' የተሰኘ ከውጭ ሀገር ገንዘብ ለመላክ የሚያስችል አዲስ መተግበሪያ ስራ አስጀምሯል። የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ፍጹም አረጋ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሀገራዊ የኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተከትሎ በሀገሪቱ የኢኮኖሚ እድገት ላይ ቁልፍ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ባንኩ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን በስኬት መሻገሩን ጠቅሰው፤ በቀጣይ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ለሚደረገው ጉዞ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ አስታውቀዋል፡፡ ዛሬ ይፋ የተደረገው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ዲያስፖራው ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኝ ከማስቻሉም ባለፈ፣ ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን ለመከላከልና የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ግኝት ለማሳደግ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዝዳንት ተወካይና የኮርፖሬት አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ኤፍሬም መኩሪያ በበኩላቸው፤ ባንኩ በየወቅቱ አሰራሩን በማዘመን ቀልጣፋና ውጤታማ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ባንኩ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት ላይ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። ስራ ላይ የዋለው መተግበሪያ የባንኩን የዲጂታል ጉዞ ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑን ጠቅሰው በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሚገኙ ደንበኞችን ይበልጥ የሚያስተሳስርና የሐዋላ ሂደትን የሚያቀላጥፍ መሆኑን ተናግረዋል። መተግበሪያው በኢትዮጵያ የፋይናንስ ስርዓት ባለው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ ትልቅ ለውጥ የሚያመጣ መሆኑን መተግበሪያውን ከንግድ ባንክ ጋር በመተባበር ያበለጸገው የስታር ፔይ ዋና ሥራ አስፈጻሚ በሱፍቃድ ጌታቸው ገልጸዋል። መንግስት ለቴክኖሎጂ ኩባንያዎች የፈጠረው ምቹ ሁኔታ መሰል ፈጠራዎች እንዲበራከቱ ማድረጉን ጠቅሰው፣ በቀጣይም ሌሎች የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ለማበልጸግ እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
የአምስት ሚሊየን ኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና የዲጂታል ክህሎት እንድናጎለብት ምቹ ሁኔታ ፈጥሮልናል
Jan 20, 2026 169
አዲስ አበባ፤ ጥር 12/2018(ኢዜአ)፦ የአምስት ሚሊየን ኢትዮ ኮደርስ ሥልጠና ከዘመኑ ጋር አብረን መራመድ የሚያስችለንን የዲጂታል ክህሎት እንድናጎለብት ምቹ ሁኔታን ፈጥሮልናል ሲሉ በመዲናዋ የኮደርስ ሰልጣኞች ገለጹ። ወጣቶች የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎታቸውንና እውቀታቸውን እንዲያዳብሩ መንግስት የአምስት ሚሊየን ኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መርሃ ግብር ዘርግቶ ብዙዎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል፡፡ ኢዜአ ስልጠናውን በመውሰድ ተጠቃሚ የሆኑ ወጣቶችንና የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶች ማህበርን አነጋግሯል። ማህበሩ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመተባበር ወጣቶች የዲጂታል እውቀታቸውን እንዲያሳድጉ የሚያስችል ስልጠና እንዲወስዱ እያገዘ እንደሚገኝም አስታውቋል። ወጣት ደረጄ ማሞ ማህበሩ የአምስት ሚሊየን ኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና የምንወስድበትን ምቹ ሁኔታን ፈጥሮልናል ብሏል፡፡ በማህበሩ እገዛ የዲጂታል ክህሎቱን ለማሳደግ የሚያግዘውን የኮደርስ ስልጠና በመውሰድ ራሱን ለማሻሻል መዘጋጀቱን አስታውቋል፡፡ በዚህም ከኮደርስ መርሃ ግብሮች መካከል አንዱ የሆነውን ዌብ ፕሮግራሚንግ በመምረጥ ስልጠና እየወሰደ እንደሚገኝ ተናግሯል፡፡ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ህይወት ገብረእግዚአብሄር በበኩሏ ከኢትዮ ኮደርስ የስልጠና አይነቶች አንዱ የሆነውን አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መውሰዷን ገልጻለች። ስልጠናው የዲጂታል ክህሎቷን ለማሳደገ አቅም እየፈጠራላት መሆኑንና ይህንንም በእለት ከእለት የስራ እንቅስቃሴዋ ጥቅም ላይ ለማዋል ጥረት እያደረገች መሆኑን ተናግራለች። በርካታ ሀገራትና ግለሰቦች በዲጂታል ቴክኖሎጂ በመታገዝ ስራዎቻቸውን እያከናወኑ መሆኑን የገለጸው ፋሲል ጉልላት እሱም ራሱን በቴክኖሎጂ ለማብቃት የአንድሮይድ የኮደርስ ስልጠና እየወሰደ መሆኑን ተናግሯል። ወጣቶች ያለንን የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎትና እውቀት ለማዳበር እንደ ሀገር የሚፈጠሩ ምቹ ሁኔታዎች ልንጠቀም ይገባል ብሏል። የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶች ማህበር ፕሬዚዳንት ወጣት በረከት ቢርቢርሳ በበኩሉ፤ ወጣቶች የስራ እድል ፈጣሪና ተጠቃሚ እንዲሆኑ የኮደርስ ስልጠና ሚናው የጎላ እንደሆነ ተናግሯል። ማህበሩ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመተባበር ወጣቶች ስለ ኮደርስ ስልጠና ግንዛቤ እንዲጨብጡ ማድረጉን ጠቅሶ፤ አሁን ላይ 81ሺህ ወጣቶች የኮደርስ ስልጠና እየወሰዱ እንደሚገኙ ጠቁሟል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የአዲስ አበባን የስማርት ሲቲ ግንባታ ይበልጥ የሚያፋጥን ነው
Jan 20, 2026 144
አዲስ አበባ፤ ጥር 12/2018(ኢዜአ)፦ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የአዲስ አበባን የስማርት ሲቲ ግንባታ ይበልጥ የሚያፋጥን መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ አስታወቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ትግበራን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት፤ዲጂታል 2030 ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል እድል መፍጠር እንዲሁም በዜጎችና ተቋማት መካከል መተማመንን መገንባት ቁልፍ የስትራቴጂው ግቦች እንደሆኑ አስረድተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ቱሉ ጥላሁን (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በመዲናዋ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ወሳኝ የሆኑ የመሠረተ ልማት ሥራዎች በስኬት ተከናውነዋል። በተለይም ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በከተማዋ ውጤታማ አፈጻጸም እንደተመዘገበበት ጠቅሰው፤ ይህም ለዲጂታል 2030 ስትራቴጂ ሽግግር አስተማማኝ መሠረት መጣሉን አስታውቀዋል። በመዲናዋ በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ የአይሲቲ ፓርክ መጠናከርን ለአብነት አንስተዋል። ቀደም ሲል በዝቅተኛ ፍጥነትና በወረዳ ደረጃ ተወስኖ የነበረው የኔትወርክ ትስስር መሻሻሉን የገለጹት ምክትል ቢሮ ኃላፊው፤ በአሁኑ ወቅት ሰማንያ ስድስት የመንግሥት ተቋማት በሲቲ ኔት (City Net) መሠረተ ልማት መገናኘታቸውን አስታውቀዋል። በተጨማሪም በከተማዋ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እና የፋይዳ ብሔራዊ መታወቂያ ተደራሽነት የስትራቴጂው ውጤት መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ በከተማዋ የመንግሥት አገልግሎቶችን ሙሉ በሙሉ ዲጂታላይዝ በማድረግ ዜጎች ባሉበት ሆነው ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ መሰረት መጣሉን ገልጸዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የአዲስ አበባን የስማርት ሲቲ ግንባታ ይበልጥ የሚያፋጥንና የዜጎችን ሕይወት የሚያቀል መሆኑን ተናግረዋል፡፡፡ ስትራቴጂው ዜጎች የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ብቻ ሳይሆኑ፣ አዳዲስ የዲጂታል መፍትሔዎችን የሚያመነጩ ፈጣሪዎች እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥርም አመልክተዋል። በአጠቃላይ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አዲስ አበባን ዘመናዊና የበለጸገች ስማርት ሲቲ የማድረግ ራዕይን እውን እንደሚያደርግ አስታውቀዋል፡፡
ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟን ለማስጠበቅ ለዲጂታል ዲፕሎማሲ ልዩ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች ነው
Jan 20, 2026 130
አዲስ አበባ፤ ጥር 12/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዘመኑን የቴክኖሎጂ ውጤቶች በመጠቀም የሀገርን ገጽታ ለማስተዋወቅ እንዲሁም ብሔራዊ ጥቅሟን ለማስጠበቅ ለዲጂታል ዲፕሎማሲ ልዩ ትኩረት በመስጠት እየሰራች መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለፀ። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዲጂታል ዲፕሎማሲ ዳይሬክተር ስላባት ማናዬ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ዲጂታል ዲፕሎማሲ የአንድን ሀገር ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ በስትራቴጂያዊ መንገድ ጥቅም ላይ እየዋለ የሚገኝ ወሳኝ መሣሪያ ነው ብለዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የተተገበረው ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ለዲጂታል ዲፕሎማሲ ስራ ምቹ ምህዳር መፍጠሩንም አስታውሰዋል። ዳይሬክተሩ አክለውም ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የመሰረተ ልማት ዝርጋታ ላይ ትኩረት የሚያደርግ በመሆኑ ለዘርፉ ትልቅ ዕድል ይዞ እንደሚመጣ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ የአርቲፊሻል ኢንተሊጀንስ የልህቀት ማዕከል ለመሆን የምታደርገው ጉዞ ዘርፉን በከፍተኛ ሁኔታ የሚደግፍ መሆኑን ጠቅሰዋል። በቀጣይ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንሲ አማካኝነት ተገልጋዮች ወደ ቆንስላዎች በአካል መሄድ ሳያስፈልጋቸው በስልካቸው አገልግሎት የሚያገኙበት አሰራር እንደሚዘረጋም ጠቁመዋል። በህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ጉብኝት ወቅት ይፋ የተደረገው የዳታ ማዕከል ግንባታም ዲጂታል ዲፕሎማሲውን ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ነው የተናገሩት። ኢትዮጵያ በሁለትዮሽና በባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ ያላትን ተመራጭነት አንስተውም፤ ሀገሪቱ ለመካከለኛው ምስራቅ፣ ለእስያና ለአውሮፓ ያላት አማካይ መገኛ እና ለቀይ ባህር ያላት ቅርበት ሁነኛ የዲፕሎማሲ አጋር ያደርጋታል ብለዋል። የቱሪዝም ዲፕሎማሲ ስራም በዲጂታል ዲፕሎማሲ በኩል እየተከናወነ እንደሚገኝ ጨምረው ገልፀዋል። ለዚህም ተፈጥሯዊና ስትራቴጂያዊ ጸጋዎች እንዲሁም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተገነቡት የቱሪዝም መዳረሻዎችን በዲጂታል አማራጮች ለዓለም የማስተዋወቅ ስራን በአብነት ጠቅሰዋል። 21ኛው ክፍለ ዘመን የትርክት የበላይነትን ለመቆጣጠር የሚደረግ የመረጃ ውድድር ያየለበት ወቅት መሆኑንም ዳይሬክተሩ አስገንዝበዋል። በሚቀያየረው የቴክኖሎጂ አውድ ውስጥ ተዋናይ ለመሆን ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ መረጃን በዲጂታል ዲፕሎማሲው በመተንተንና ቀድሞ በመተንበይ ለሀገራችን ብሔራዊ ጥቅም መከበር ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
በባህር ዳር ከተማ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ዘመናዊ የህዝብ ማጓጓዣ አውቶቡሶች ሥራ ጀመሩ
Jan 17, 2026 121
ባህር ዳር፣ጥር 9/2018(ኢዜአ)፦የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር በከተማዋ የሚስተዋለውን የትራንስፖርት ችግር ለማቃለል በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ዘመናዊ የህዝብ ማጓጓዣ አውቶቡሶችን ሥራ አስጀመረ። ዛሬ የአውቶቡሶቹ ርክክብ ሥነ ስርአት የተካሄደው የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፣የምስራቅ እዝ ዋና አዛዥና የቀጠናው የፀጥታ ግብረ ሃይል ሰብሳቢ ሌተናል ጄነራል መሀመድ ተሰማና ሌሎች ሥራ ሃላፊዎች በተገኙበት ነው። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው በዚህ ወቅት እንደገለጹት፦ የከተማዋን ዘመናዊነት ከሚያረጋግጡ ተግባራት መካከል ዘመናዊና የተሳለጠ የትራንስፖርት አገልግሎት አንዱ ነው። በዚህም ከተማ አስተዳደሩ ዘመኑን የዋጁና በኤሌክትሪክ የሚሰሩ አስር አውቶብሶችን በመግዛት ዛሬ ሥራ ማስጀመሩን ገልፀዋል። ይህም የከተማዋን ህዝብ የትራንስፖርት ችግር ከመፍታት ባለፈ የቱሪዝም ማዕከልና የኢንቨስትመንት ተመራጭ ከተማ ለማድረግ የተጀመረውን ሥራ እንደሚያጠናክር አስረድተዋል። በተለይም አውቶቡሶቹ በከተማዋ በኮሪደር ልማት ከተገነባው ሰፊ የአስፋልት መንገድ ጋር የተጣጣመ የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ዘመኑን የሚመጥንና በአነስተኛ ክፍያ ለህብረተሰቡ የትራንስፖርት አገልግሎት ማቅረብ ወሳኝና የከተማ እድገት መገለጫ እንደሆኑም አመልክተዋል። በከተማዋ ከዚህ ቀደም ከ20 በላይ አውቶብሶች ለህብረተሰቡ አገልግሎት ሲሰጡ እንደነበር ጠቁመው፣ የኤሌክትሪክ አውቶብሶች መጨመር የባህር ዳርን ስማርት ከተማነት ለማረጋገጥ የተያዘው ግብ ለማሳካት ያግዛል ብለዋል። የቢኬጅ (በላይነህ ክንዴ ግሩፕ) ባለቤትና የቦርድ ሰብሳቢ አቶ በላይነህ ክንዴ በእለቱ እንደገለጹት፥ ቢኬጅ እንደሀገር በተለያዩ የልማት ሥራዎች ላይ በንቃት እየተሳተፈ ያለ ድርጅት ነው ። በሀገር አቀፍ ደረጃ ትኩረት የተሰጠውን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ለማሳካትም አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማስገባት ጭስ አልባና ለብዙ ጊዜ አገልግሎት የሚሰጡ አውቶቡሶችን በመገጣጠም እያከፋፈለ ይገኛል ብለዋል። አውቶቡሶቹ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ እንደመሆናቸው መጠን ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ መሳካት ጉልህ ፋይዳ እንዳላቸው ገልጸው፣ በሀገር ውስጥ መመረታቸው መለዋወጫ በቀላሉ ለማግኘት እንደሚያስችል ተናግረዋል። በአውቶቡሶቹ ርክክብ ላይ የተገኙት አማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በኤሌክትሪክ የሚሰሩትን አውቶብሶች ሥራ አስጀምረዋል። በሥነ-ስርዓቱ ላይ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር) ጨምሮ ሌሎች አመራሮችና የከተማዋ ነዋሪዎችም ተገኝተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ