ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
የስማርት አዳማ ፕሮጀክት ግቦችን ለማሳካት ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቷል
Jan 2, 2026 77
አዳማ፤ ታህሳስ 24/2018(ኢዜአ)፦ የስማርት አዳማ ፕሮጀክት ግቦችን ለማሳካት ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ማስፋፋት ላይ ትኩረት መሰጠቱን የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ ገለፁ። በአዳማ ከተማ ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማጠናክርና ህብረተሰቡን የፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ ያለመ የምክክር መድረክ ተካሂዷል።   የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ በወቅቱ እንደገለፁት የስማርት አዳማ ፕሮጀክትን ለማሳካት የሚደረገው ጥረት አካል የሆነው ፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቷል። ይህም የከተማዋን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶች ዲጂታላይዝድ በማድረግ ህብረተሰቡ ባለበት ቦታ ሆኖ የመንግስት አገልግሎትን በተቀላጠፈና አስተማማኝ በሆነ መንገድ ለማግኘት ያግዛል ብለዋል። የመንግስት አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝድ ማድረግ ተገልጋዩ ከመሬት ሀብት አስተዳደርና አጠቃቀም ጋር የሚያነሳቸው ጥያቄዎችን፣ የገቢ ግብር፣ የትራንስፖርት አገልግሎትና የከተማዋን ፀጥታ በካሜራ በመቆጣጥር ምላሽ መስጠት እንደሚያስችል ጠቁመዋል።   የስማርት ሲቲ አካል የሆነው የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሁሉንም አገልግሎቶች ዲጂታላይዝድ በማድረግ በአንድ ቦታ ለማግኘት የጎላ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ብለዋል። የዲጂታል ቴክኖሎጂው ስርአትም ሌብነትና የመሬት ምዝበራን በማስቀረት የከተማዋን ገቢ በማሳደግ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማቶች እንዲሳለጡ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። በውይይቱ ከተሳተፉ የአዳማ ከተማ ነዋሪ ሀሰን ጂማ እንደገለፁት የከተማዋ የዲጂታል አገልግሎት ጊዜና ገንዘባቸውን ቆጥቦላቸዋል። ዲጂታል አገልግሎቱ ከፋይዳ መታወቂያ ጋር መተሳሰሩ ቀደም ሲል በከተማዋ ይስተዋሉ የነበሩ ብልሹ አሰራሮችን በመቅረፍ የተሻለ አገልግሎት እንድናገኝ የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ በላቸው ደምሴ ናቸው።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት ነው
Jan 2, 2026 63
ወልዲያ፤ ታህሳስ 24/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት መሆኑን የኢንፎርሜሽ ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ታኅሣሥ 11 ቀን 2018 ዓ.ም የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ስትራቴጂ ይፋ በማድረግ የዲጂታል 2025 ክንውን ደግሞ በስኬት መጠናቀቁን መግለፃቸው ይታወሳል። በሰሜን ወሎ ዞን ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂና የኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት መሆኑን ገልጸዋል። የአይሲቲ ባለሙያ የሆኑት ታደሰ አብዬ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በዘርፉ ጽኑ መሰረት ያኖረ ስኬታማ ስራ መሆኑን ተናግረዋል። የስትራቴጂው መተግበር በበርካታ ተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥና የአሰራር ቅልጥፍናን፣ የቁጥጥርና ተጠያቂነት አሰራርን በማስፈን እንዲሁም ብልሹ አሰራርን መከላከል አስችሏል ብለዋል። ይህም ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በማሳካት የአገራችንን ሁለንተናዊ እድገት ዳር ለማድረስ መሰረት የጣለ በመሆኑ በጋራ ልንረባረብ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። የኮሙኒኬሽን ባለሙያው አሰፋ መስፍን፤ በኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት እመርታዊ ለውጥና ማንሰራራት ማምጣቱን ገልጸው ለቀጣዩ እቅድ የላቀ ስኬት መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። በተለይም በአርተፊሻል ኢንተለጀንስና ሌሎች የቴክኖሎጂ ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶችን አንስተው በፋይናንስ ተቋማትና ሌሎች ተቋማት የታየውን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማሳያነት ጠቅሰዋል። በመሆኑም የዲጂታል ልማት ስትራቴጂ ለፍጥነት፣ ፈጠራና ለሀገር እድገት ወሳኝ በመሆኑ ለ2030 ስትራቴጂክ እቅድ ስኬት ሁላችንም የድርሻችንን መወጣት አለብን ብለዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስኬቶች ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 መሠረት ናቸው
Jan 2, 2026 65
ጅግጅጋ፤ ታህሳስ 24/2018(ኢዜአ)፦ በአገልግሎት አሰጣጥና በዜጎች ላይ መሰረታዊ ለውጥ ያመጣው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ ስኬቶች ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 መሰረት መሆናቸውን በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉ ባለሙያ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ማጠናቀቅያ እና በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት ላይ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ መቶ በመቶ በሚባል ደረጃ የተሳካ መሆኑን መግለጻቸው ይታወሳል ። በስትራቴጂው በግብርና፣ በማዕድን ብሎም በኢንዱስትሪው እንደተገኘው ስኬት በዲጂታሉ ዘርፍም መገኘቱን አንስተው ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስኬት ፅኑ መሰረት እንደሚሆነው ማመላከታቸውም እንዲሁ። በዚሁ ጉዳይ ላይ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ የአይ ሲ ቲ ዳይሬክቶሬት የኔትወርክ ቡድን መሪ ታደለ ነጋ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የሀገርን ሁለንተናዊ ልማትና እድገትን ለማሳካት ጠንካራ መሰረት ያኖረ መሆኑን ገልጸዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በተቋማት እና በአገልግሎት አሠጣጥ ዘርፈ ብዙ ስኬቶች የተመዘገበበት መሆኑንም አክለዋል። በተለይም የተቋማት የአሠራር ሥርዓት እና ለዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ ለውጦች የተገኙበት መሆኑን ተናግረዋል። በክፍያ ሥርዓት፣ በትምህርት፣ በጤና፣ በግብርናና በሌሎችም ሴክተሮች በዲጂታል ዘርፉ በተሠሩ ሥራዎች አበረታች ስኬቶች መገኘታቸውን ገልጸዋል። ዜጎች የተለያዩ ወጪዎችን የእጅ ስልካቸውን ተጠቅመው በቀላሉ ክፍያዎችን መፈጸም የሚያስችሉ የሲስተም ሥርዓቶች መዘርጋታቸውን ጠቅሰዋል። በጤና ተቋማት ከወረቀት ንክኪ ነጻ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን ገልጸው ይህም የዜጎችን የጤና መረጃዎች ወደ ዲጂታል ሲስተም በማስገባት እና ጤናቸውን ለመጠበቅ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው አንስተዋል። በትምህርት ዘርፉም አገር አቀፍ የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና በበይነመረብ መስጠት መቻሉን ገልፀው ይህም ኩረጃን ማስቀረቱንና ተማሪዎች የተለያዩ ዕድሎችን መጠቀም እንዲችሉ የዲጂታል ማጎልበት ኢንሼቲቭ ተግባራዊ መደረጉን ገልጸዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት በዘርፉ የተገኙት ስኬቶችን መሠረተ በማድረግ ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ውጤታማነት የዘርፉ ባለሙያዎች ድጋፍ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የወንጀል መከላከልና ምርመራ ሥራን ወደ ላቀ የቴክኖሎጂ ምዕራፍ በሚያሸጋገር መልኩ ይተገበራል
Jan 2, 2026 64
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የወንጀል መከላከልና ምርመራ ሥራን ወደ ላቀ የቴክኖሎጂ ምዕራፍ በሚያሸጋገር መልኩ እንደሚተገበር የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት፤ ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል ዕድል መፍጠር፣ በዜጎችና ተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት የስትራቴጂው ቁልፍ ትልሞች መሆናቸውን መግለጻቸው ይታወቃል። የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ለወንጀል መከላከልና ምርመራ ሥራዎች ቴክኖሎጂን በስፋት እየተጠቀመ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የተለያዩ መተግበሪያዎችን በራስ አቅም በማበልጸግ እንዲሁም ከአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ እና ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በፖሊስ ሥራዎች ላይ ለውጥ እንዲመዘገብ ማስቻሉንም ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅት ሕብረተሰቡ የወንጀል ጥቆማዎችንና የሚፈልጋቸውን መረጃዎች በአካል ፖሊስ ጣቢያ ሳይገኝ በሞባይል ስልኩ ብቻ የሚያገኝበት ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ኮሚሽነር ጄኔራሉ ገልጸዋል። አክለውም ከአንድ ወር በኋላ ሰው አልባ የፖሊስ ጣቢያ (Smart Police Station) በአዲስ አበባ ሥራ እንደሚጀምር ጠቁመዋል። የጣት አሻራን አውቶሜት የማድረግ ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቁመው፤ የጦር መሣሪያ ምዝገባን ከፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር ቁጥጥር የሚደረግበት ሥርዓት መዘርጋቱንም ጠቅሰዋል።   ፌደራል ፖሊስ በ2030 የወንጀል ምርመራ፣ መከላከልና የውስጥ አሠራሮችን በቴክኖሎጂ ሙሉ በሙሉ ለማዘመን በቁርጠኝነት እየሠራ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም ፖሊሳዊ አገልግሎቶችን በላቀ ደረጃ የሚያጎለብት መሆኑን አስረድተዋል። በቀጣይም 196 ሀገራት የሚሳተፉበት የዓለም አቀፉ ፖሊስ (ኢንተርፖል) ጉባኤ በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ጠቁመው፤ ተቋሙ በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና የዘመነ መሆኑን ለማሳየት በትኩረት እየተሠራ መሆኑን አረጋግጠዋል።
ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መሳካት ዘመኑን የዋጁ የሥልጠና ፕሮግራሞች እየተከፈቱ ነው
Jan 2, 2026 53
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መሳካት በዘርፉ ብቁ ባለሙያ ለማፍራት ዘመኑን የዋጁ የሥልጠና ፕሮግራሞች እየተከፈቱ መሆኑ ተገለጸ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ባስጀመሩበት ወቅት፤ ስትራቴጂው ተደራሽ፣ ፍትሐዊ እና አስተማማኝ የዲጂታል ምኅዳር መፍጠር ላይ ማተኮሩን ገልጸዋል።   የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በቴክኒክና ሙያ መስክ አበረታች ለውጥ እንዲመዘገብ ዐቅም ፈጥሯል። ለአብነትም ስትራቴጂው ኢንስቲትዩቱ የአሰለጣጠን ሂደቱን ዘመኑን በዋጀ መልኩ እንዲቃኝና የሰዎችን የዲጂታላይዜሽን ግንዛቤ እንዲጎለብት መሰረት መጣሉን አንስተዋል። ኢንስቲትዩቱ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ሊያሳካቸው ከያዛቸው ዓላማዎች ጋር በማስተሳሰር ለመተግበር የሚያስችለውን የሠነድ ዝግጅት እያደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂክ ግቦችን ለማሳካት የተሻለ የዲጂታል ክኅሎት ያላቸው ሰልጣኞችን ማፍራት በትኩረት የሚሠራበት ጉዳይ መሆኑን አመላክተዋል። አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የሳይበር ሴክዩሪቲና ሌሎች የሥልጠና ዓይነቶች ለስትራቴጂው መሳካት ሚናቸው የላቀ መሆኑን ለአብነት አንስተዋል። በተጨማሪም በዲጂታል ክኅሎት የበለጸገ ባለሙያ ለማፍራትና የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በተሻለ መንገድ ለማበልጸግ ተቋሙ ራሱን በግብዓትና በአደረጃጀት እያጠናከረ እንደሚገኝም ነው ያስታወቁት።
ባህላዊ እሴቶችን በጥናት በማስደገፍ ለጋራ ትርክት ግንባታ ለማዋል በቅንጅት እየተሰራ ነው
Jan 1, 2026 172
አምቦ ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦ ባህላዊ እሴቶችን በጥናት በማስደገፍ ለጋራ ትርክት ግንባታ ለማዋል በቅንጅት እየሰራ መሆኑን የኦሮሞ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት አስታወቀ። በሀገር በቀልና ኪነጥበብ ላይ ያተኮረ ኮንፍረንስ በአምቦ ዩኒቨርሲቲ ተካሂዷል፡፡   የኦሮሞ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት ምክትል ዳይሬክተር አቶ ዝናቡ አስራት በወቅቱ እንዳሉት ኢንስቲትዩቱ የኦሮሞ ህዝብ ታሪክና ባህል እሴቶችን በጥናት በማስደገፍ ለጋራ ትርክት ግንባታ ለማዋል እየሰራ ነው፡፡ የመደጋገፍ የባህል እሴቶችን በጥናትና ምርምር በማስደገፍ ለትውልድ ለማስተላለፍና ይበልጥ ለማስተዋወቅ ከሌሎች ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በቅንጅት መስራታቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡   የባህል እሴቶቹ ለትውልድ እንዲተላለፉና በትምህርት ስርአት ውስጥ እንዲካተቱ እንዲሁም በመጽሃፍት እንዲታተሙ ምክረሀሳብ መቅረቡን ተናግረዋል፡፡ በጥናትና ምርምር ተደግፈው የተጻፉ የህትመት ውጤቶችም ለህብረተሰቡ እንዲደርሱ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ የሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የጥናትና ምርምር ማእከል ዳይሬክተር ሳሙኤል ሌይኩን (ዶ/ር) ፤ ለአራተኛ ጊዜ በተካሄደው በሀገር በቀል የኪነጥበብ ኮንፍረንስ ላይ የኦሮሞን ህዝብ የመተጋገዝ ባህል በኪነጥበብ ስራዎች ላይ የተቃኙበትን አውድ የሚያስረዳ ጥናት ይዘው መቅረባቸውን ተናግረዋል።   የምርምር ውጤቶች ትውልዱ ባህላዊ እሴቱን በመረዳት ባህሉንና ቋንቋውን እንዲያዳብር ትልቅ አስተዋጽኦ አላቸው ብለዋል፡፡ የአምቦ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ባይሳ ለታ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው ሀገር በቀል የባህል እሴቶችን በማጥናት ለህብረተሰብ ግንባታ የሚውሉበትን ሂደት ለማሳለጥ ከኪነ ጥበብ ስራዎች ጋር ለማስተሳሰር መሰራቱን ተናግረዋል፡፡   ባህልን ከኪነ ጥበብ ስራዎች ጋር ማቀናጀት በሀገራዊ እድገት ውስጥ ትልቁን ሚና የሚጫወት በመሆኑ የኮንፍረንሱ መካሄድ ይህን ለማሳካት ልምድ የሚወሰድበት ጭምር መሆኑን ጠቁመዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ መምህርና ተመራማሪ ፕሮፌሰር ተሰማ ታአ፤ የባህልና የታሪክ እሴቶችን በማጥናት ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማዋል መሰረታዊ ጉዳይ ነው ብለዋል።   ባህላዊ እሴቶችን ለትውልድ ለማስተላለፍም መሰል የባህል የምርምር ኮንፍረንሶች ተጨማሪ አቅም መሆናቸውን አስረድተዋል። የኦሮሞ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት ከአምቦ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ባዘጋጀው ኮንፍረንስ ላይ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ ተመራማሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፈዋል፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ የጥናትና ምርምር ሥራዎች ማከናወኑን አጠናክሮ ይቀጥላል
Jan 1, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ የጥናትና ምርምር ሥራዎች ማከናወኑን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጸ፡፡ ዩኒቨርሲቲው የተመሠረተበትን 75ኛ ዓመት የአልማዝ ኢዮቤልዩ በዓል አስመልክቶ የተቋሙን አጠቃላይ ሀገራዊ አበርክቶ የሚዳስሱ ጥናታዊ ጽሑፎች የቀረቡበት ሲምፖዚየም ተካሂዷል። ዩኒቨርሲቲው ባለፉት 75 ዓመታት በሀገሪቷ የሰው ኃይል ልማት፣ በጤና፣ በፖለቲካ፣ በማኅበራዊና በኢኮኖሚ ዘርፎች ለሀገር ያበረከተውን አስተዋጽኦ የተመለከቱ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡ የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ጄይሉ ዑመር (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ዩኒቨርሲቲው ለሀገር ዕድገት ወሳኝ ሚና የተጫወቱ ምሁራን ያፈራ አንጋፋ ተቋም ነው ብለዋል።   ተቋሙ በቀጣይም ጥራት ያለው የሰው ኃይል ለማፍራትና ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ የምርምር ሥራዎችን ለማከናወን ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማኅበራዊና ኢኮኖሚ ምርምር ተቋም ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ዓለሙ መኮንን በሲምፖዚየሙ ላይ ባቀረቡት ጽሑፍ፤ ዩኒቨርሲቲው ባለፉት አሥርተ ዓመታት በሀገሪቷ የሥራ መስኮች የተሰማሩ ብቁ ባለሙያዎችን በማፍራት ረገድ ግንባር ቀደም መሆኑን ገልጸዋል።   በቀጣይ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር የሚራመድ የሰው ኃይል በማፍራት ረገድ ጠንካራ ሥራ ሊሠራ እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡   የታሪክ ምሁሩ ደቻሳ አበበ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ተቋሙ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በማስተዋወቅ ረገድ ያለበትን ኃላፊነት ሊወጣ እንደሚገባ አመልክተዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ 32 ሚሊዮን ማሳዎች በዲጂታል የመረጃ  ሥርዓት ተደራጅተዋል
Jan 1, 2026 94
አርባ ምንጭ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦በሀገር አቀፍ ደረጃ 32 ሚሊዮን ማሳዎች በዲጂታል የመረጃ ሥርዓት መደራጀታቸውን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የገጠር መሬት አስተዳደር ሥርአትን ከፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ጋር ለማስተሳሰር ያለመ ክልል አቀፍ የንቅናቄ መድረክ ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የግብርና ሚኒስቴር የገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ትዕግስቱ ገብረመስቀል እንዳሉት፣ የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ የሚያግዙ የግብርና መረጃዎችን እንደ የአፈር መረጃ፣ የአየር ፀባይ ሁኔታ፣ የማዳበሪያ አቅርቦት እና የመሬት መጠቀሚያ ስርአት አገልግሎትን ዲጂታላይዝድ ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ ነው። ይህም ግብርናውን ለማዘመንና የአርሶና አርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚያግዝ ገልጸዋል። ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያም የግብርና መረጃዎችን ዲጂታላይዝድ በማድረግ የአርሶና የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያግዝ ነው ብለዋል። አርሶና አርብቶ አደሮች የመሬት ይዞታቸውን ዲጂታላይዝድ ለማድረግ በተደረገው ጥረት በእስካሁኑ ሂደት በሀገር አቀፍ ደረጃ 32 ሚሊዮን ማሳዎች በዲጂታል ስርአት እንዲደራጁ መደረጉንም አቶ ትዕግስቱ ገልጸዋል። በተለይም አርሶና አርብቶ አደሮች የመሬት ይዞታቸውን በአግባቡ ለማስተዳደር እንዲችሉና ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ ከፋይናንስ አገልግሎት ጋር ማስተሳስር አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው፣ ለዚህም ዲጂታል የፋይዳ መታወቂያ ያግዛቸዋል ብለዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መሬት አስተዳደር ቢሮ ሃላፊ አቶ ሰብስቤ ቡናቤ፤ በክልሉ የአርሶና አርብቶ አደሩን የመሬት አስተዳደር ወደ ዲጂታል ስርአት በማስገባት ተጠቃሚነቱን ለማላቅ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል።   የክልሉ አርሶና አርብቶ አደሮች የዲጂታል መሬት አስተዳደር ስርአቱ ተጠቃሚ ለመሆንም የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ሊኖራቸው እንደሚገባ አመልክተዋል። የመሬት አስተዳደር ስርአትን ለማዘመን በተደረገ ጥረት በ869 ሺህ 211 አባወራና እማወራዎች እጅ ያለ ከ2 ሚሊዮን በላይ መሬቶች በዲጂታል ስርአት እንዲደራጅ መደረጉንም ገልጸዋል። ይህን አጠናክሮ ለመቀጠልም በሚቀጥሉት አንድ መቶ ቀናት በክልሉ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን አርሶና አርብቶ አደሮች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተናግረዋል።   ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ አገልግሎቶችን በማቀላጠፍ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት እያገዘ ነው ያሉት ደግሞ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የምዝገባ አስተባባሪ ደጀኔ ገብሬ ናቸው። ዲጂታል መታወቂያ ለአርሶና አርብቶ አደሮች የብድር አገልግሎቶችን በማግኘት በስራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ያስችላል ብለዋል። ለአንድ ቀን በተዘጋጀው የንቅናቄ መድረክ ላይ የፌደራል፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ የዞኖችና የወረዳ አመራሮች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
ጠንካራ የቴክኖሎጂ ዐቅምን ለመፍጠር የምርምር ሥራዎችን ማጠናከር ይገባል-ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ
Jan 1, 2026 118
አዲስ አባበ፤ታኅሣስ 23/2018 (ኢዜአ)፡-ጠንካራ የቴክኖሎጂ ዐቅምን ለመፍጠር ዘመን ተሻጋሪ የምርምር ሥራዎችን መሥራት ያስፈልጋል ሲሉ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ አስገነዘቡ። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት የምርምርና ልማት ፖሊሲ ምረቃና የማዕከል ምሥረታ ተካሂዷል።   ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ በዚሁ ወቅት፤ ጥናትና ምርምር የአንድን ሀገር ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ወታደራዊ ዐቅምን በመገንባት የማድረግና የመፈፀም ችሎታን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ከፍተኛ ሚና አለው ብለዋል። ከተቋም አልፎ ለሀገራችን ብሎም ለአኅጉራችን ሁለንተናዊ ዕድገት የበኩላቸውን አስተዋፅኦ የሚያበረክቱ የምርምር ሥራዎችን በመሥራትና በማዳበር አዳዲስ ግኝቶችን ልናበለፅግ ይገባል ሲሉም በአጽንኦት ገልጸዋል። ታላቅ ሀገርና ተቋም መገንባት የሚቻለው ሁል ጊዜ አዳዲስ ሐሳቦችን በማፍለቅ፣በማዳበር፣ በመከታተልና በመመራመር ነው ሲሉም አብራርተዋል። በዚህም መሠረት ችግር ፈቺ እና የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም በዘላቂነት የሚያስጠብቁ ጠንካራ የቴክኖሎጂ ዐቅሞችን በመፍጠር ዘመን ተሻጋሪ የልማትና የምርምር ሥራዎችን በትኩረት መሥራት ያስፈልጋል ብለዋል።   የመከላከያ ዋር ኮሌጅ አዛዥ ሜጄር ጄኔራል ቡልቲ ታደሰ በበኩላቸው፤ ማዕከሉ ለሠራዊቱ የትራንስፎርሜሽን ጉዞ ስኬት የማይተካ ሚና እንደሚጫወት ይታመናል ብለዋል። በተጨማሪም ለዘመናዊ ሠራዊት ግንባታ እንደ ማዕዘን ድንጋይ ሆኖ ያገለግላል ማለታቸውን የመከላከያ ኦንላይን ሚዲያ ለኢዜአ የላከው መረጃ ያመላክታል። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በደኅንነትና በቴክኖሎጂው ዘርፍ ቀዳሚ የሐሳቦችና የፈጠራዎች ማዕከል በመሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ተቋም እንዲሆን አስቻይ ሁኔታዎችን ይፈጥራል ሲሉም ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት ስትራቴጂ የመፍጠርና መተግበር አቅም የታየበት ነው
Jan 1, 2026 104
መቀሌ ፤ታህሳስ 23/2018 (ኢዜአ) ፡-የኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት ስትራቴጂ የመፍጠርና መተግበር አቅም የታየበት መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ተናገሩ። የ "ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ስትራቴጂ ትግበራን ታኅሣሥ 11 ቀን 2018 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በይፋ ማስጀመራቸው ይታወቃል። ለእቅዱ ትግበራም የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስኬት በመሰነቅ በቀጣይ በዘርፉ የኢትዮጵያን እድገትና ማንሰራራት የማስቀጠል ግብ የተቀመጠለት ነው። በዚህም መሰረት ተደራሽነትን፣ ለዜጎች እኩል እድል መፍጠርንና በዜጎችና በተቋማት መካከል መተማመንን የማጎልበት ዓላማ በማንገብ ለስኬቱ ተግባራዊ እንቅስቃሴ እየተደረገ ይገኛል። ከዚሁ ጋር በተገናኘ ኢዜአ በትግራይ ክልል መቀሌ ያነጋገራቸው በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር አይ ሲቲ ኤጀንሲ የዘርፉ ባለሙያዎች የዲጂታል አገልግሎት ከፈጣንና ዘመናዊ አገልግሎትም ባለፈ ለብልሹ አሰራር ምክንያቶች ዘላቂ መፍትሄ የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል። ከባለሙያዎቹ መካከል የአይ ሲቲ ባለሙያ የሆኑት አቶ እያሱ ተካ፤ የዲጂታል ልማትና ተግባራዊ እንቅስቃሴ ዘመኑ የሚጠይቀው የሀገራት መወዳደሪያ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ ያለፉት ዓመታት ትግበራና ቀጣይ የተያዘው እቅድ በዘርፉ የሌሎች አገራት ተከታይ ከመሆን ይልቅ የመፍጠርና መተግበር አቅም የታየበት መሆኑን ገልጸዋል። የዲጂታል አገልግሎት አሰራር ፈጣን አገልግሎት ከመስጠቱም ባለፈ የብልሹ አሰራር ምክንያት የሚሆኑ ክፍተቶችን የሚዘጋ ነው ብለዋል። የሃርድዌርና ሶፍት ዌር ጥገና ከፍተኛ ባለሙያው ዮውሃንስ ለአከ በበኩሉ የደረስንበት ዘመን የመፍጠርና የመፍጠን በመሆኑ በዲጂታል ዓለም ተወዳዳሪ ለመሆን በዚሁ ልክ መጓዝ ይኖርብናል ሲል ተናግሯል። ኢትዮጵያ በዘርፉ ልማት እያደረገች ያለችው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን አንስቶ ለቀጣይ እቅዶች የላቀ ስኬት የሁላችንም ጥረትና እገዛ ያስፈልጋል ብሏል። በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በዘርፉ የተከናወነው ተግባር ከፍተኛ የሚባል ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን የገለፀው ደግሞ ሌላኛው የሶፍትዌር እና ሃርድዌር ጥገና ባለሙያ ወጣት አረጋይ ገብረመስቀል ነው። በዲጂታል ልማት የብዙ ተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ ከወረቀት ነፃ እንዲሆን መደረጉን አንስቶ የባንኮችና የቴሌኮም አገልግሎትም መሰረታዊ ለውጥ የመጣበት ስለመሆኑ አንስቷል። በመሆኑም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ እቅድ በተሳካ ሁኔታ ተግባራዊ እንዲሆን የመንግስት ጥረት እንዳለ ሆኖ የባለሙያዎችና የሚመለከታቸው አካላት ጥረት ሊታከልበት ይገባል ብሏል።  
በሶማሌ ክልል 200 ሺህ ሰዎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን አጠናቀዋል
Jan 1, 2026 54
ጅግጅጋ፣ ታህሳስ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል 200 ሺህ ሰዎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ማጠናቀቃቸውን የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ገለጸ። የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ምክትል ቢሮ ሃላፊ አቶ መሀሙድ ሁሴን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ የ5 ሚሊዮን የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና 322 ሺህ ሰዎችን ተደራሽ ለማድረግ ታቅዶ ሲሰራ ቆይቷል። በዚህም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤትና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ መምህራን፣ የመንግስት ሰራተኞች እና ሌሎች ከቴክኖሎጂው ጋር ቅርበትና ፍላጎት ያላቸው ዜጎች ስልጠናውን በመስጠት በክልሉ 200 ሺህ ዜጎች ስልጠናውን አጠናቀዋል ብለዋል። የኢትዮ ኮደርስ ኢንሼቲቭ በዘርፉ አገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ብቁ ዜጋ ለማፍራት እንዲሁም የሥራ ዕድልን ለመፍጠር ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በቀሪው የበጀት ዓመቱ ወራትም ከ122 ሺህ በላይ ሰዎችን ለማሠልጠን ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸው፤ ስልጠናውን በክልሉ በሚገኙ የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እና በበየነ መረብ መውሰድ እንደሚቻል ጠቁመዋል። ተማሪ ኩሬሽ መሀሙድ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስደው ካጠናቀቁት መካከል ስትሆን ስልጠናው የቴክኖሎጂ እውቀቷን እንደጨመረው አንስታለች። ስልጠናውን በበይነመረብ መውሰድ እንደሚቻል ከተነገረኝ በኋላ ስልጠናውን በመውሰድ አጠናቅቄያለሁ ብላለች። ሌላኛዋ ተማሪ ፋጡማ ሹክር በበኩሏ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናውን በመውሠድ የቴክኖሎጂ እውቀቷን ማዳበር የሚያስችላትን በዳታ አናላይሲስ በማጠናቀቅ ሰርተፊኬት ማግኘቷን ተናገራለች። ተማሪ ነስሪን ሁሴን በበኩሏ ስልጠናውን በበይነመረብ በመውሰድ ቴክኖሎጂን የመጠቀም አቅም እንዳሳደገች ተናግራለች።  
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን የዲጂታል አድራሻ በሁሉም ከተሞች ማስፋት ያስችላል
Jan 1, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን ብሔራዊ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት በሁሉም ከተሞች ማስፋት እንደሚያስችል የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ጂኦ ስፓሻል ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ታህሳስ 11 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ይፋ ማድረጋቸው ይታወቃል።   በወቅቱ ባስተላለፉት መልዕክትም ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ተደራሽነትን የማስፋት፣ ለዜጎች እኩል ዕድል የመፍጠር፣ የዜጎችና ተቋማትን መተማመን የማጎልበት ቁልፍ ትልሞች እንዳሉት አጽንኦት ሰጥተዋል። የሕዝብ መገልገያ ዲጂታል መሠረተ ልማቶችን በማስፋት የዜጎችን የዕለት ከዕለት ኑሮ በሰው ተኮር ዲጂታል ሥርዓት ማሻሻል እንደሚያስፈለግ አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ ለኢዜአ እንገለጹት፤ የከተሞችን የመሠረተ ልማት ግንባታ ለማሳለጥ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት መሠረት ነው። የዲጂታል አድራሻ መሠረተ ልማት የከተማ ይዞታን በዲጂታል መለያ በሚገባ በማስቀመጥ በዘመናዊ ሥርዓት የሚተዳደሩ ከተሞችን ለመገንባት ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ገልጸዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መነሻነት ብሔራዊ የዲጂታል አድራሻ መሠረተ ልማትን የማስፋት ሥራ በወሳኝ የትኩረት መስክ መያዙን ጠቁመዋል።   የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት በበርካታ ከተሞች በተለያየ ደረጃ በትግበራ ላይ እንደሚገኝም ዋና ዳይሬክተሩ አንስተዋል። ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትልሞች የብሔራዊ የዲጂታል አድራሻን ማስፋት በግልጽነት ላይ የተመሠረተ የአገልግሎትና የአስተዳደር ሥርዓት ለመፍጠር ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል። ስትራቴጂው በሀገር አቀፍ ደረጃ በከተሞች የተጀመረውን ብሔራዊ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት በሁሉም ከተሞች ለማስፋት ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ አንስተዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የከተሞችን ሁለንተናዊ የልማት ትስስር በማሰናሰል ዘመናዊ የአገልግሎትና የአስተዳደር ሥርዓት መሰረት መጣሉንም አስታውሰዋል። በቀጣይም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የኮሙኒኬሽን መገናኛ መሠረተ ልማቶችን በራስ አቅም በማልማት ፍትሐዊ የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነትን ለማስፋት እንደሚሰራ አስረድተዋል። #DigitalEthiopia2030
በኢትዮጵያ የአረንጓዴ ትራንስፖርትን ለማስፋፋት የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ ነው
Dec 31, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 22/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የአረንጓዴ ትራንስፖርትን ለማስፋፋት የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን ገለጹ። በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ለአምስት ተከታታይ ቀናት የተካሄደው ሁለተኛው የብክለት ቀናሽ እንቅስቃሴ(ግሪን ሞቢሊቲ) አውደ ርዕይና ፎረም 2025 ተጠናቋል። በአውደ ርዕይና ፎረሙ የመዝጊያ ሥነ-ሥርዓት ላይ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን፤ የዘንድሮው ዓውደ ርዕይ ዓላማውን ያሳካና ውጤታማ መሆኑን ገልጸዋል። በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የተካሄዱ የውይይት መድረኮችም በርካታ አካላትን ያገናኙና ውጤታማ መረጃዎች የተለዋወጡባቸው መሆናቸውን ጠቁመዋል። በአውደ ርዕዩ ኢትዮጵያውያን በዘርፉ ላይ የላቁ የቴክኖሎጂ የፈጠራ ሥራዎችን በማቅረብ ሻጮችና ሸማቾች የተገናኙበት ትልቅ መድረክ መሆኑን ተናግረዋል።   መጪው ጊዜ ለኢትዮጵያ ብሩህ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ሀገሪቱ በአረንጓዴ ትራንስፖርት ዘርፍ የጀመረቻቸውን ውጤታማ ሥራዎች አጠናክራ እንደምትቀጥልም አረጋግጠዋል። በአሁኑ ወቅት የአረንጓዴ ትራንስፖርትን ለማስፋፋት የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዓውደ ርዕዩ አዳዲስ የአረንጓዴ ትራንስፖርት ቴክኖሎጂዎች ለዕይታ መቅረባቸውንና ዘርፉ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም ያለውን ፋይዳ በተመለከተም የጋራ ግንዛቤ የተፈጠረበት እንደሆነ ገልጸዋል። ለአውደ ርዕዩ መሳካት አስተዋጽኦ ላደረጉ ተሳታፊዎች ምስጋና አቅርበው፤ በመጪው ዘመን በፈጠራው ዘርፍ የተሻሉ ሥራዎች እንደሚጠበቁም አመልክተዋል። ዓውደ ርዕዩ በቀጣይም ይበልጥ እንዲሳካ በትኩረት እንደሚሠራ አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ ከአየር ንብረት ተጋላጭነት ለመውጣት የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭን ጨምሮ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን በማስፋፋት በኩል ውጤታማ የአረንጓዴ ልማት እርምጃዎችን እየወሰደች እንደምትገኝም በዚሁ ወቅት ተመልክቷል።
በከተማው ዲጂታል ቴክኖሎጂ ለዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እያገዘ ነው
Dec 31, 2025 64
ጎንደር፤ ታህሳስ 22/2018(ኢዜአ)፦ በጎንደር ከተማ ዲጂታል ቴክኖሎጂ የዜጎችን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ በመፍታት ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ምቹ ምህዳር እየፈጠረ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ቻላቸው ዳኘው ተናገሩ፡፡ የከተማ አስተዳደሩ መሬት መምሪያ ዘመናዊ የመሬት ይዞታ መረጃን በዲጂታል የመረጃ ስርዓት መምራት የሚያስችለውን የካዳስተር አሰራር በይፋ በማስመረቅ ዛሬ አስጀምሯል፡፡ በምረቃው የተገኙት ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ቻላቸው እንደተናገሩት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ኢንሼቲቭ ከተሞች በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፈ የዲጂታል አገልግሎት እንዲሰጡ መሰረት የጣለ ነው።   ዲጂታል ቴክኖሎጂ ዜጎች ማናቸውንም የመንግስት አገልግሎቶች ፈጣንና ቀልጣፋ በሆነ መልኩ እንዲያገኙ አስቻይ ሁኔታ የሚፈጥር ነው ብለዋል፡፡ ገቢ የመሰብሰብ አቅምን በማሳደግ ልማትና እድገትን ለማፋጠን አዎንታዊ ሚና እንዳለውም ነው የተናገሩት፡፡ የመሬት ይዞታ መረጃ ስርዓቱ ዲጂታል መደረጉ በከተማዋ ህገ ወጥ ግንባታንና የመሬት ወረራን ለመቆጣጠር ብሎም በዘርፉ ይስተዋሉ የነበሩ የሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከል የጎላ ፋይዳ አለው ብለዋል፡፡   የካዳስተር ሥርዓት የከተማውን የመሬት ሀብት በአግባቡ ቆጥሮና ለይቶ በማደራጀት አልምቶ ለመጠቀም ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል ያሉት ደግሞ የከተማ አስተዳደሩ መሬት መምሪያ ሃላፊ ትዛዙ በጽሃ ናቸው፡፡ የካዳስተር ስርዓት በተተገበረባቸው ከ2010 እስከ 2017 ባሉት ዓመታት ከ21ሺህ በላይ የመሬት ይዞታዎችን የመለየትና መረጃ የማሰባሰብ ሥራዎችን በቴክኖሎጂ ታግዞ ማከናወኑን ተናግረዋል፡፡ በተያዘው በጀት ዓመትም ከ15ሺህ በላይ ይዞታዎችን መረጃ ማሰባሰቡን ገልጸው፣ ሁሉንም ይዞታዎች ወደ መረጃ ቋት በማስገባት በአሁኑ ወቅት ይዞታቸው ለተረጋገጠላቸው ነዋሪዎች ዲጂታል ካርታ የመስጠት ሥራ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡ በዛሬው እለት ዲጂታል ካርታ ከተረከቡ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ሃና ማለደ በሰጡት አስተያየት ዲጂታል ካርታ ዜጎች አስተማማኝ የይዞታ ማረጋገጫ አንዲኖራቸው ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል፡፡   ዲጂታል ካርታ ከዚህ ቀደም በመሬት ይዞታ ይረጋገጥልኝ ጥያቄ ላይ ያጋጥሙ የነበሩ ብልሹ አሰራሮችን የሚያስቀርና ከእንግልት የሚታደግ በመሆኑ መደሰታቸውን የገለጹት ደግሞ አቶ አህመድ ለጋስ ናቸው።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የመዲናዋን የኢንዱስትሪ ተወዳዳሪነት ለማላቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል
Dec 31, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 22/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የመዲናዋን የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ለማላቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ስኬታማነት የማጠናቀቂያና የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ማብሰሪያ መርሃግብር መካሄዱ ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅትም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል ዕድል መፍጠር፣ የዜጎችና ተቋማትን መተማመን ማጎልበት ቁልፍ ትልሞች መሆናቸውን አጽንኦት ሰጥተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን የሚያሳልጥ መሰረት ተጥሏል። የዲጂታል ዓለም በሰው ሰራሽ አስተውሎት የፈጠረው ከፍተኛ አቅም ለኢንዱስትሪ የምርት ጥራትና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት መልካም አጋጣሚዎችን እየፈጠረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የዲጂታላይዜሽን ሥርዓትም ለመዲናዋ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ቁጥርና የምርታማነት አቅም በማላቅ ወሳኝ ሚና እየተወጣ መሆኑን አስረድተዋል። በአዲስ አበባ ከተማም ከ3 ሺህ 824 በላይ ኢንዱስትሪዎች በዲጂታል ቴክኖሎጂ ሥርዓት የታገዘ ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ ምርት ለገበያ በመቅረብ እመርታዊ ለውጥ እያመጡ መሆኑን አስገንዝበዋል። በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የሚተገበረው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ቁልፍ ትልሞችም የኢንዱስትሪ ምርታማነትን በማላቅ ለዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ግዙፍ የውድድር መድረክ እየሆነ በመጣው የዲጂታላይዜሽን ሥርዓት ውስጥ መሪ ተዋናይ ለመሆን ዘመኑ የደረሰበትን የቴክኖሎጂ ውጤት መጠቀም እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂም በአዲስ አበባና በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለተሰማሩ አልሚዎች ምርታማነት ወሳኝ አቅም እንደሚፈጥር አንስተዋል።
በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ሁሉም ሆስፒታሎች የዲጂታል የጤና አገልግሎት እንዲሰጡ ይደረጋል
Dec 31, 2025 99
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 22/2018(ኢዜአ)፦በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ሁሉም ሆስፒታሎች የጤና አገልግሎቶችን በዲጂታል መስጠት የሚችሉባቸው ግብዓቶች እየተሟሉ መሆኑን የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ የዜጎችን ጤናና ማህበራዊ ደህንነት ለማረጋገጥ ዓለም አቀፍና ሀገራዊ የጤና ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎችን ገቢራዊ አድርጋለች፡፡ በዚህም መከላከልን መሰረተ ባደረገው የጤና ፖሊሲዋ የእናቶችና ህፃናትን ሞት በመቀነስ በዘላቂ የልማት ግቦች የተቀመጡ ዕቅዶችን ቀድማ ማሳካት ችላለች፡፡ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ሚኒስቴሩ የጤና ተቋማትን በግብዓት በማዘመን፣ በዲጂታል የታገዘ የጤና አገልግሎት በመስጠት ዲጂታል ቴክኖሎጂን በተሻለ የሚጠቀም ተቋም ነው፡፡ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለጤናው ዘርፍ መልካም ዕድል ይዞ መምጣቱን ገልጸው፤ በስትራቴጂው ማብቂያ አብዛኞቹ የጤና ተቋማት የመረጃ ስልታቸውን ወደ ዲጂታል ሥርዓት ያስገባሉ ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ በ2030 ሁሉም ሆስፒታሎች ሙሉ በሙሉ ወረቀት አልባ አገልግሎት እንዲሰጡ አስፈላጊው የዲጂታል አገልግሎት ግብዓት እየተሟላ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የጤና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎች በማህበረሰብ አቀፍ የጤና ሥርዓት በቀበሌዎች ያለውን መረጃ በዲጂታል ሥርዓት ይዘው ሪፖርት የሚያደርጉበት አሰራር መኖሩንም ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ይህንን አሰራር ሙሉ በሙሉ ገቢራዊ በማድረግ የዲጂታል አገልግሎት በጤናው ዘርፍ የላቀ አገልግሎት እንዲኖረው ይደረጋል ብለዋል፡፡ የጤና ተቋማትን ማዕከል ያደረጉ የመረጃ ሥርዓቶች ወደ ዲጂታል ይገባሉ ያሉት ዶክተር ደረጀ፤ የጤና ባለሙያዎች ላይ ቁጥጥር የሚደረግበት አሰራር ገቢራዊ እንደሚደረግም ገልጸዋል፡፡ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ዜጎች ከቤታቸው ሆነው የጤና ምክርና አገልግሎት የሚያገኙበትን፣ ቀጠሮ የሚይዙበትን ቀላልና ቀልጣፋ እድል ይፈጥራል ብለዋል፡፡ የታካሚዎች የህክምና መረጃ በቀላሉ ማግኘት የሚያስችል የዲጂታል ስርዓት ገቢራዊ እንደሚደረግ በመጥቀስ፤የዲጂታል መረጃ ስርዓቱን የሚያሳልጡ ግብዓቶች ወደ ሀገር ቤት እየገቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ፖስታ አዳዲስ መተግበሪያዎች አሰራሩን ወደ ላቀ ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ናቸው
Dec 30, 2025 158
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 21/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፖስታ አዳዲስ መተግበሪያዎች የዲጂታል ኢትዮጵያን ስትራቴጂ ወደ ተግባር የሚቀይሩና አሰራሩን ወደ ላቀ ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ መሆናቸውን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ። ዛሬ “የሳጥን አልባ የመልዕክት አገልግሎት”(Virtual post Box) እና “የፖስታ ገበያ” የተሰኙ አዳዲስ መተግበሪያዎች ይፋ ተደርገዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በመርሃ-ግብሩ እንደገለጹት፤ መተግበሪያዎቹ ኢትዮጵያ በዘመናዊነት ጉዞዋ ለምታስመዘግበው ውጤት ማሳያ ናቸው።   በተለይም የፖስታ ገበያ መተግበሪያ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች የሚያጋጥሟቸውን የመገበያያ መሰናክሎች በማቃለል በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸውን ተወዳዳሪነት ያሳድጋል ብለዋል።   የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዳግማዊ ኃይልዬ በበኩላቸው፤ አገልግሎቱ መልዕክቶችንና ዕቃዎችን ከዓለም ጫፍ እስከ ጫፍ በማድረስ ረጅም ዘመን ያስቆጠረ መሆኑን ገልፀዋል። ዛሬ ይፋ የሆኑት መተግበሪያዎች ደግሞ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር በማቀናጀት ወደ ፊት የሚያራምዱ መሆናቸውን ነው ያብራሩት። የሳጥን አልባ የፖስታ ደንበኞች የግል የፖስታ ሳጥን ቁጥር ሳይኖራቸው የራሳቸውን ስልክ ቁጥር እንደ ፖስታ አድራሻ እንዲጠቀሙ የሚያስችል መሆኑንም ገልጸዋል።   ደንበኞች የተላከላቸው ዕቃ ወይም መልዕክት መድረሱን በስልካቸው አማካኝነት ፈጣን መረጃ ያገኛሉ። ዕቃዎችን ደንበኞች ባሉበት አድራሻ እንዲደርሷቸው በማድረግም ቀደም ሲል የነበረውን የገንዘብ ብክነትና እንግልትም የሚያስቀር መሆኑን አስታውሰዋል። አዲሱ አሰራር ድርጅቱ ካለው ረጅም ልምድ ጋር ተዳምሮ የደንበኞችን እርካታ ከፍ እንደሚያደርገው ተገልጿል።
የዲጂታል ልማትና አገልግሎት በኢትዮጵያ መሰረታዊ ለውጥና ተጨባጭ ውጤት አምጥቷል
Dec 30, 2025 125
ሆሳዕና፤ ታህሳስ 21/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ልማትና አገልግሎት በኢትዮጵያ መሰረታዊ ለውጥና ተጨባጭ ውጤት የመጣበት መሆኑን በዋቸሞ ዩኒቨርስቲ የዘርፉ ምሁራን ገለጹ፡፡ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በተለይም በተቋማት አገልግሎት አሰጣጥና በዜጎች የአኗኗር ዘይቤ ላይ የሚታይ ለውጥ የመጣበት በመሆኑ ለቀጣዩ ዕቅድ የላቀ ስኬት መስራት አስፈላጊ መሆኑንም አንስተዋል። ከዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስኬት በመነሳት ተደራሽነትን፣ ለዜጎች እኩል እድል መፍጠርንና በዜጎችና በተቋማት መካከል መተማመንን የማጎልበት ዓላማን በመሰነቅ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ይፋ መደረጉ ይታወቃል። ኢዜአ ያነጋገራቸው በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የኮምፒውተር ሳይንስ መምህርት ፀጋነሽ ሞገስ፤ በኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት በተለይም በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ መሰረታዊ ለውጥ አምጥቷል ብለዋል።   የአሰራር ፍጥነትን፣ ቁጥጥርንና ተጠያቂነትን እውን በማድረግ ለዜጎች ፍትሃዊ አገልግሎት ለመስጠት በሚደረገው ጥረት የዲጂታል አገልግሎት ትልቁን ድርሻ መያዙን አንስተዋል። የኮደርስ ስልጠና፣ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ ብሔራዊ መታወቂያ የዘርፉን አገልግሎት ይበልጥ እያሳለጡ መሆኑን አንስተው የቴሌብር፣ የባንክና ሌሎችም የተቋማት አገልግሎቶች እመርታዊ ለውጥ አምጥተዋል ብለዋል። የዲጂታል ልማት በድምሩ በኢትዮጵያ መሰረታዊ ለውጥና ተጨባጭ ውጤት የመጣበት መሆኑን ገልጸው፣ ዜጎች በአንድ ቦታ የተለያዩ አገልግሎቶችን በማግኘት እንግልትን እንዳስቀረ ተናግረዋል። ከዚህ በመነሳት በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ለማሳካት የተቀናጀ ጥረት ማድረግ ይገባል ሲሉ መምህርቷ ተናግረዋል። በዩኒቨርሲቲው የሶፍትዌር ኢንጂነሪንግ መምህር መሳይ አስቻለው፤ በ2025 የዲጂታል ኢትዮጵያ ትግበራ መሰረተ ልማትን ከመዘርጋት ጀምሮ በቴክኖሎጂ የተደራጀ ተቋምና የተሻለ ግንዛቤ ያለው ትውልድ በመገንባት ረገድ ተጨባጭ ስኬት ተመዘግቧል ብለዋል።   የኢትዮጵያን ቀጣይ እጣ ፈንታ ለመወሰን በቴክኖሎጂ ልማት ላይ መስራት ለነገ የማይባል ሥራ መሆኑን አንስተው ለተያዘው እቅድ መሳካት የሁላችንም ጥረትና ትብብር ያስፈልጋል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ በተለይ ዲጂታል 2030 እንደሀገር የተጀመረውን ራዕይ የሚያሳካ መሆኑን ገልጸው፣ ዜጎች በተለይ ወጣቱ በቴክኖሎጂ ብቁ እንዲሆን የተጀመሩ ሥራዎች ለዚህ ስኬት ጉልህ አስተዋጽኦ አላቸው ብለዋል። የኢትዮጵያን እድገትና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት እውን ለማድረግ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የልማት ግብ ማሳካት እንደሚገባም አጽእኖት ሰጥተዋል። በተለይ ቴክኖሎጂ የሀገርን ኢኮኖሚና ማህበረሰቡን ለማነቃቃት ካለው ጠቀሜታ አንጻር ታይቶ ዘርፉን ለማሳደግ የተጀመረው ሥራ መጠናከር እንዳለበት አመልክተዋል።
የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ መርሃግብር በዲጂታል ስነ ምህዳር ንቁ ተሳትፎ ለማድረግ ያስችላል
Dec 30, 2025 122
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 21/2018(ኢዜአ):- የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያዊያን ኮደርስ መርሃግብር በዲጂታል ስነ-ምህዳር ውስጥ ንቁ ተሳትፎ ለማድረግ የሚያስችል ክህሎት እየፈጠረላቸው መሆኑን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ገለጹ። ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት መሰረተ ልማትና አስቻይ ስርዓት ከመዘርጋት በተጨማሪ የዲጂታል ክህሎት ያለው ማህበረሰብ አስፈላጊ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐምሌ 16 ቀን 2016 ዓም የአምስት ሚሊየን ኮደርስ ኢኒሼቲቭን ማስጀመራችው ይታወሳል። ኢኒሼቲቩ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስና የኢትዮጵያ መንግስታት የሚተገበር ሲሆን፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያሉ 5 ሚሊዮን ወጣቶች በኦንላይን የኮዲንግ ስልጠና የሚወስዱበት ነው። ስልጠናው በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ ዳታ ሳይንስ እና አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ መሠረታዊ የዲጂታል ክህሎት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው። ኢዜአ ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና የኮተቤ ትምህርት ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንዳሉት የኮደርስ ስልጠና ዘመኑ የሚጠይቀውን የዲጂታል ክህሎት ለማጎልበት መሰረት የሚሆን ነው። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢንፎርሜሽን ሲስተም ተማሪ አርሴማ መንግስቱ የኮደርስ ስልጠና ካለክፍያ የቀረበ መሰረታዊ የዲጂታል ክህሎትን ለመገንባት ዕድል መፍጠሩን ተናግራለች። የኮደርስ ስልጠና ለዲጂታላይዜሽን መፋጠን ወሳኝ በመሆኑ ሁሉም ሰው ስልጠናውን ሊከታተል እንደሚገባ ገልፃለች። በዩኒቨርሲቲው ሌላኛዋ የኢንፎርሜሽን ሲስተም ተማሪ ፅዮን ምስጋናው በበኩሏ የኮደርስ ስልጠና ለሁሉም ሰው በተመቸ አግባብ የተዘጋጀ ነው ብላለች። በኮደርስ ስልጠና ያገኘችው መሰረታዊ የዲጂታል ክህሎት ለመደበኛ ትምህርቷ እገዛ እንዳደረገላትም ነው ያስረዳችው። ስልጠናው ለቴክኖሎጂ አጠቃቀም መመሪያ በሚሆንና ሁሉም ሰው ሊረዳ በሚችለው አግባብ የተዘጋጀ መሆኑን የተናገረችው ደግሞ የኢንፎርሜሽን ሲስተም ተማሪዋ ቤተልሄም ሰለሞን ነች። የኮተቤ ትምህርት ዩኒቨርሲቲ የስፖርት ሳይንስ ተማሪ ገለታ ካፎ እንዳለው ስልጠናው በኮምፒውተርም ሆነ በስልክ ኦንላይን መከታተል የሚቻል ነው።   ተማሪዎች ስልጠናውን በመከታተል የዲጂታል ክህሎታቸውን ማሳደግ አለባቸው ያለው የዩኒቨርሲቲው የትምህርት አመራርና አስተዳደር ተማሪ ዲቃባ ጎንጂ ነው።      
የጎንደር ከተማ የዲጂታል አድራሻ ስርዓት በመጪው ጥር ወር ስራ ይጀምራል
Dec 30, 2025 114
ጎንደር፤ ታህሳስ 21/2018(ኢዜአ)፦ በጎንደር ከተማ የዲጂታል አድራሻ ስርዓትን በመጪው ጥር ወር ስራ ለማስጀመር ዝግጅት መጠናቀቁን የከተማ አስተዳደሩ የስማርት ሲቲ ማስተባባሪያ ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ከጎንደር ከተማ አስተዳደር ጋር ጥቅምት 2018 ዓም ጎንደር ከተማን የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል የፕሮጀክት ስምምነት በተፈረመበት ወቅት ፕሮጀክቱ ጥር ወር 2018 ተጠናቅቆ ወደ ስራ እንደሚገባ መገለጹ ይታወሳል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ የስማርት ሲቲ ማስተባባሪያ ጽህፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ይልቃል ሙሉአለም(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤቱ ከስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ጋር በመቀናጀት የዲጂታል አድራሻ ሰርዓት ትግበራን ለማሳካት ሲሰራ ቆይቷል። ስርዓቱ መንግስት ከተሞችን ለማዘመን የጀመራቸውን የዲጂታላይዜሽን ስትራቴጂ አጠናክሮ የሚያስቀጥል መሆኑንም ገልጸዋል። ባለፉት ሶስት ወራት ከኢኒስቲትዩቱ ጋር በመተባበር በቴክኖሎጂ የተደገፉ የዲጂታል ዳታዎችን የማሰባሰብና የማደራጀት ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን አውስተዋል። በጂፒኤስና በዲጂታል ካርታ የተደራጀው የዲጂታል የአድራሻ ስርዓት በከተማው መሬት ላይ ያሉ ሀብቶችን፤ መሰረተ ልማቶችን ቤቶችንና የዋና ዋና መንገዶች ቋሚ አድራሻዎችን በቀላሉ ለተጠቃሚው አቅጣጫ የሚያመላክት ነው ብለዋል። የዲጂታል ቴክኖሎጂውን ወደ ተግባር ማሸጋገር የሚያስችሉ የሳተላይት ምስልና መረጃ መሰብሰብን ጨምሮ ከ60ሺህ በላይ የመንገድና የትራፊክ እንዲሁም የቦታ መረጃ የማደራጀት ስራዎች መጠናቀቃቸውን ገልጸዋል፡፡ ከ74ሺህ በላይ ህንጻዎችና መኖሪያ ቤቶችን ጨምሮ 682 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የዲጂታል የመንገድ ኔትወርክ መረጃዎች ተሰብስበው ወደ ሲስተም መግባታቸውንም አረጋግጠዋል፡፡ ስርዓቱ ለዲጂታል ኢኮኖሚው እድገት መፋጠን፤ ለዘመናዊ ከተማ ግንባታ፤ ለቱሪዝም እንዱስትሪ ማደግ፣ የትራንስፖርት ዘርፉን ለማዘመንና የከተማውን ጸጥታና ደህንነት በቴክኖሎጂ ለመቆጣጠር ጠቀሜታ አለው ብለዋል፡፡ ነዋሪዎች የኤሌክትሪክ፣ የውሃና የቴሌ ኮም የጥገና አገልግሎቶችን ባሉበት ቦታ ሆነው እንዲያገኙና አገልግሎት የሚሰጡ አካላትም በፍጥነት ደርሰው ምላሽ እንዲሰጡ አጋዥ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የእሳት አደጋ እና ድንገተኛ የአምቡላንስ እርዳታ አገልግሎቶችን ነዋሪዎች በቀላሉ ማግኘት እንዲችሉ የዲጂታል አድራሻ ስርዓቱ የጎላ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ በከተማው የሚገኙ የመንግስት ተቋማት፣ የግል መኖሪያና የንግድ ቤቶችም ዲጂታል መለያ ቁጥር እንደተዘጋጀላቸው ጠቁመው ፕሮጀክቱ ጥር 2018 ዓም ተመርቆ ስራ እንደሚጀመርም ገልጸዋል፡፡ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ኢኒሼቲቭ ውጤት የሆነው የዲጂታል አድራሻ ስርዓት የከተማውን እድገትና ልማት የሚጠቁሙ አዳዲስ መረጃዎች በየሦስት ወሩ ወደ ሲስተም የማስገባት ስራ እንደሚቀጥል ታውቀዋል፡፡ የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት በኢትዮጵያ 100 ከተሞችን ተደራሽ የሚያደርግ የዲጂታል አድራሻ ስርዓት ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ መሆኑን ጥቅምት 7/2018 ጎንደር ከተማን የዲጂታል አድራሻ ስርዓቱ ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል ፕሮጀክት የመግባቢያ ሰነድ በተፈረመበት ወቅት መግለጹ ይታወሳል፡፡ በአማራ ክልል ደብረ ብርሃን እና ኮምቦልቻ ከተሞች የቴክኖሎጂው ተጠቃሚ መሆናቸውንና በደሴና ወልዲያ ከተሞችም ፕሮጀክቱን ተግባራዊ ለማድረግ መታቀዱን የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር በላቸው ፀሐይ መናገራቸውም እንዲሁ፡፡ በወቅቱ የጎንደር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ቻላቸው ዳኘው እንዳሉት አስተዳደሩ ለፕሮጀክቱ ተፈጻሚነት ከኢንስቲትዩቱ ጋር በቅርበት ይሰራል። ጥር 2018ዓም በከተማው በድምቀት ለሚከበረው የጥምቀት በዓል ቴክኖሎጂውን ተግባራዊ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን መናገራቸውም ይታወሳል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም