ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
መፍትሔ አፍላቂ የቴክኖሎጂ ፈጣሪ ወጣቶች
Jan 5, 2026 49
በጀነራል ዊንጌት ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የማኑፋክቸሪንግ ትምህርት ክፍል አሰልጣኝ ወርቁ ፈንታሁን ከጓደኛው ጋር በመሆን በኢትዮጵያ ያለውን የዶሮ እርባታ ስራን ዘመናዊ ማድረግ የሚያስችል ቴክኖሎጂ ፈጥረዋል። ዘመናዊ የዶሮ ማርቢያ ቤት(ኬጅ) ለመፍጠር ያነሳሳቸው በባህላዊ መንገድ የሚከናወነውን አሰራር ለማዘመን በማሰብ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊው የዶሮ ኬጅ በተወሰነ አካባቢ ላይ በርካታ ዶሮዎችን ለማርባትና ዶሮዎቹን በንጹህ እና ጤንነታቸው በተጠበቀ ቦታ ማርባት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የሚገኘውን የእንቁላል ምርት ሳይሰበር በቀላሉ መሰብሰብ የሚቻልበትን እድልም ይፈጥራል ብለዋል። በቀጣይም ቴክኖሎጂው ለዘርፉ ውጤታማነት ከሚኖረው ፋይዳ አንጻር የማስተዋወቅና በስፋት ተመርቶ ወደ ገበያ እንዲቀርብ እንደሚሠሩ ጠቁመዋል። አካል ጉዳተኞችን በቀላሉ መመገብና ፈሳሽ ነገሮችን ማጠጣት የሚያስችል ሮቦት የሰራው ደግሞ በጀነራል ዊንጌት ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ የኢንዱስትሪያል ኤሌክትሮኒክስ ቴክኖሎጂ የደረጃ አራት ተመራቂ ተማሪ ዳግም ጋርጠው ነው። ሮቦቱ ያለምንም የሰው ንክኪ አካል ጉዳተኞች በቀላሉ በሚጠቀሙበት መልኩ የተሠራ ነው ብሏል። ስራው ውጤታማ እንዲሆን ኮሌጁ የግብዓት፣ የሙያ እና ሌሎች ድጋፎች እንዳደረገለትም ተናግሯል። በኮሌጁ የቴክኖሎጂ ልማትና የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን አገልግሎት ምክትል ዲን ደሜ መርሻ በአሰልጣኞችና በሰልጣኞች ቅንጅት ውጤታማ የፈጠራ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል። የመኖ መፍጫ፣ የዘመናዊ ዶሮ ኬጅ እና የፕላስቲክ መፍጫና ማቀነባበሪያ እንዲሁም ፕላስቲኩን ወደ ተለያየ ምርት መቀየር የሚችሉ ማሽኖች በኮሌጁ ተሰርተው ጥቅም ላይ ከዋሉ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ውጤቶች መካከል መሆናቸውን አብራርተዋል። የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅርበት እየሰራ እንደሚገኝና ፈጠራዎቹን የማስተዋወቅ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር(ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ተቋማት ቴክኖሎጂ ፈጣሪ ባለሙያዎችን እንዲሁም ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን እንዲያመነጩ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ የምታስገባቸውን የተለያዩ የቴክኖሎጂ ውጤቶች በሀገር ውስጥ ለመተካት፣ አዳዲስ ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን የመፍጠር ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ገልፀዋል። በቴክኒክና ሙያ የሚሰሩ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ስራዎች በሀገር ልማት ላይ አበረታች ወጤት እያመጡ መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል። ኢንስቲትዩቱ ሀገራዊ የክህሎት ማበልፀጊያ ፕሮግራም ተግባራዊ በማድረግ የቴክኖሎጂ ፈጠራ ያላቸውን ዜጎች ውጤታማ እንዲሆኑ ከተለያዩ አካላት ጋር በመሆን እየደገፈ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
የዲጂታል ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው ያስችላል
Jan 4, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦የዲጂታል ሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው በማድረግ ትክክለኛ ፖሊሲ መቅረጽ የሚያስችል መሆኑን የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ገለጸ፡፡ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት በአዋጅ ቁጥር 1370/2017 መሰረት ከፌደራል እስከ ታችኛው የአስተዳደር እርከን ድረስ ራሱን የቻለ አደረጃጀት ያለው ሆኖ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የማከናወን፣ የመምራት፣ የማስተባበር፣ የመደገፍ፣ የምዝገባ መረጃዎችን የማስተዳደር እና የማደራጀት፣ በብሔራዊ ደረጃ በመረጃ ቋት አደራጅቶ የመያዝ ሀላፊነት ተሰጥቶታል። አገልግሎቱ በተሰጠው ስልጣን መሰረተ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ውክልና በመስጠት በመዲናዋ ሁሉም ወረዳዎች የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ማከናወን ጀምሯል፡፡ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ቢቂላ መዝገቡ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የወረቀት አሰራርን በመቀየር አንድ ሰው አንድ ማንነት እንዲኖረው ያደርጋል፡፡ ከዚህ ቀደም በነበረው የማኑዋል/የወረቀት አሰራር አንድ ሰው ሁለት ቦታ የልደት፣ የሞትና መሰል የወሳኝ ሁነት የምስክር ወረቀት ያወጣ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ በዚህም በተጭበረበረ መረጃ የተሰሩ የወሳኝ ሁነት መረጃዎች መንግስት ለሚያሳልፋቸው የፖሊሲ ውሳኔዎች አስቸጋሪ ሆነው መቆየታቸውን ገልጸዋል፡፡ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ የባዮሜትሪክና ባዮግራፊክ መረጃ እንደሚይዝ ገልጸው፤ የባዮሜትሪክ መረጃዎችን ከብሔራዊ መታወቂያ ጋር እንዲተሳሰር ይደረጋል ብለዋል፡፡ በዚህም አንድ ሰው አንድ ሆኖ የሚታወቅባትን ኢትዮጵያ መፍጠር የሚያስችል እንቅስቃሴ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የባዮሜትሪክና ባዮግራፊክ መረጃዎችን በማቀናጀት የአንድን ሰው ትክክለኛ ማንነት የሚገልጹ መሆናቸውን የገለጹት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፤ የአንድን ሰው ዜግነት መለየትም ያስችላሉ ብለዋል፡፡ እነዚህ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ መረጃዎችን በኩነት ምዝገባና እና በብሄራዊ መታወቂያ /ፋይዳ/ አማካኝነት መሰብሰብ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ማከናወን የሚያስችል መተግበሪያ በኢትዮጵያ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት አማካኝነት ለምቶ ወደ ሥራ መግባቱንም ተናግረዋል፡፡
የዲጂታል ግብይት ሥርዓት የንግድ እንቅስቃሴን አቀላጥፏል
Jan 4, 2026 82
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እያደገ የመጣው የዲጂታል ግብይት ሥርዓት የንግድ እንቅስቃሴን ከማቀላጠፍ ባለፈ ከመጭበርበርና ከእንግልት እየታደጋቸው መሆኑን የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ። ነዋሪዎቹ መጪዎቹን የገና እና የጥምቀት በዓላት ግብይታቸውን በቴሌብር እና በሞባይል ባንኪንግ በመጠቀም ያለምንም እንግልት እያከናወኑ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት መካከል አቶ ገዛህኝ መካሻ እንደገለጹት፤ የዲጂታል ግብይት ሥርዓቱ በፈጠረው ምቹ ሁኔታ ማንኛውንም ክፍያ በቴሌብርና በሞባይል ባንኪንግ እንደሚፈጽሙ ገልጸዋል። ይህም ጉልበትንና ጊዜን ከመቆጠብ ባለፈ፣ ተንቀሳቃሽ ገንዘብ በመያዝ ከሚገጥሙ ስጋቶችና ከአጭበርባሪዎች ራሳቸውን ለመከላከል እንዳስቻላቸው ጠቁመዋል። በመሆኑም ለመጪዎቹ በዓላት የሚገዟቸውን ቁሳቁሶች በዲጂታል መንገድ እየፈጸሙ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ዶክተር ሳሮን ሲሳይ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል የነበሩ የክፍያ አገልግሎቶች በእንግልት የተሞሉና ጊዜን በአግባቡ ለመጠቀም የማይመቹ እንደነበሩ አስታውሰዋል። አሁን ላይ ግን እያንዳንዱን አገልግሎት በዲጂታል መንገድ መፈጸም መቻሉ ሕይወትን በእጅጉ ቀለል እንዳደረገው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እያሳየች ያለውን ፈጣን ዕድገት ለማስቀጠል የዲጂታል ዓለምን መቀላቀሏ የሚያስደስት መሆኑን የገለጹት ደግሞ መምህርት ፍሬሕይወት ለማ ናቸው። የዲጂታል ግብይት ሥርዓቱ ጥሬ ገንዘብ የመያዝ ልማዴን በማስቀረት ሁሉንም አገልግሎት በስልኬ እንዳገኝ አስችሎኛል ሲሉም አክለዋል። የኢትዮ ቴሌኮም የሞባይል መኒ ቢዝነስ ዋና ኦፊሰር አቶ ብሩክ አድሃና፤ ተቋሙ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የዲጂታል ሕልም እውን ለማድረግ በትጋት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል። እንደ ኦፊሰሩ ገለጻ፤ባለፉት አራት ዓመታት ከሀምሳ ሰባት ሚሊዮን በላይ በሆኑ የዲጂታል ክፍያ ደንበኞች አማካኝነት ከስድስት ትሪሊዮን ብር በላይ ግብይት ተከናውኗል። መጪዎቹን የገናና የጥምቀት በዓላት ምክንያት በማድረግም ደንበኞች የዲጂታል ግብይቶችንም ሆነ ሌሎች አገልግሎቶችን ያለምንም መቆራረጥ እንዲያከናውኑ አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን አረጋግጠዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት መረጋገጥ የላቀ ሚና ይጫወታል
Jan 4, 2026 83
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት ይበልጥ መረጋገጥ የላቀ ሚና እንደሚጫወት የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ ገለጹ፡፡ የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ፤ ጥራት ያለውና ፍትሐዊ የትምህርት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የዲጂታል ቴክኖሎጂን አማራጮች በአግባቡ መጠቀም ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ ዓለም አቀፋዊውን የዕድገት ፍጥነት ተከትሎ በትምህርት መስኩ ዕውቀትና ክህሎቱ የዳበረ ማኅበረሰብን ለመፍጠር ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ጉልህ አሻራ አሳርፏል ነው ያሉት። በተለይም የመማር ማስተማር ሂደቱን በማዘመንና የፈተና አሰጣጥ ሥርዓቱን ዲጂታላይዝ በማድረግ የፈተና ደኅንነት እንዲጠበቅ ማድረጉንም ገልጸዋል፡፡ ስትራቴጂው ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሀገሪቱን የዲጂታላይዜሽን ጉዞ የሚደግፉ የሥልጠና መስኮችን እንዲከፍቱና በዘርፉ ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት የሚያስችሉ ግብዓቶች እንዲሟሉ ምቹ መደላድል መፍጠሩንም አክለዋል። መንግሥት የሀገሪቱን ብልጽግና ለማረጋገጥ የጀመረውን የማዘመን ሥራ ይበልጥ ለማሳለጥ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ተግባራዊ ማድረጉንም ገልጸዋል፡፡ ይህ ስትራቴጂ ዜጎች በዲጂታል ቴክኖሎጂ አማራጮች ታግዘው ባሉበት ቦታ ሆነው እንዲማሩ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ስትራቴጂው የትምህርት ተደራሽነትን ከጥራት ጋር በማጣመር ረገድም የላቀ ፋይዳ እንደሚኖረው ጠቁመዋል፡፡ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘርፍ የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራትና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ከኢንዱስትሪው ጋር ይበልጥ ለማቀራረብ በትኩረት ይሠራል ብለዋል፡፡ ይህም ተማሪዎች በቴክኖሎጂው ረገድ ተግባር ተኮር ዕውቀትና ክህሎት እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። በተጨማሪም በዲጂታላይዜሽን ዙሪያ የሚከናወኑ የምርምር ውጤቶች ለተግባራዊ ጥቅም እንዲውሉ በማድረግ የትምህርት ዘርፉ ለስትራቴጂው ስኬት የሚጠበቅበትን ሀገራዊ ኃላፊነት እንደሚወጣ አረጋግጠዋል።
ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ኢትዮጵያ ለያዘችው የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬታማነት ቁልፍ ሚና አለው
Jan 4, 2026 86
ጅግጅጋ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ኢትዮጵያ ለያዘችው የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬታማነት ቁልፍ ሚናን የሚጫወት መሆኑን የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና አስተባባሪ ዮዳሄ አርአያስለሴ ገለጹ። የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም 2ኛው ዙር "ፋይዳ ለኢትዮጵያ" በሚል መሪ ሐሳብ የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ በጅግጅጋ ከተማ ተካሄዷል። በመርሃ ግብሩ መክፈቻ ላይ የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና አስተባባሪ ዮዳሄ አርአያስለሴ እንደገለጹት፤ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ኢትዮጵያ ለያዘችው የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬታማነትም ቁልፍ ሚናን የሚጫወት ነው። ዜጎች ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያን በመውሰድ የዜግነት መብታቸውን መጠቀም እንዳለባቸውም ጥሪ አስተላልፈዋል። የሱማሌ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኢብራሂም ኡስማን፤ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ለሀገር ዕድገት ያለው ጠቀሜታ ከፍተኛ እንደሆነ ገልጸው በክልሉ ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡ ለዜጎች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶችን ተደራሽ ለማድረግ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ አስፈላጊ በመሆኑ ሁሉም ዜጋ እንዲወስድ ሃላፊው አሳስበዋል። የዛሬው የሩጫ ውድድርም የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ሂደትን ከማነቃቃት ባለፈ በስፖርት ተወዳዳሪ ወጣቶችን ለማፍራት ትልቅ ዕድል መሆኑን አንስተዋል። በጎዳና ላይ የሩጫ ውድድሩ የክልሉ አመራሮች፣ አትሌት ኮማንደር ደራርቱ ቱሉ፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ አትሌቶች እና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እንዲሁም የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
የኢትዮ-ቴሌኮም ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬት ገንቢ ሚና ይወጣል
Jan 3, 2026 117
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮ-ቴሌኮም ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ስኬት ገንቢ ሚና እንደሚወጣ የኢትዮ-ቴሌኮም ቺፍ ቴክኖሎጂ ኦፊሰር ታሪኩ ደምሴ ገለጹ። ኢትዮ ቴሌኮም 130ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን በማስመልከት ያዘጋጀውን ሁለት ዘመናዊ የኤሌክትሪክ መኪና ሽልማቶች ለአሸናፊ ደንበኞቹ አስረክቧል፡፡ ኩባንያው በሽልማት መርሃ-ግብሩ ላይ ተጨማሪ ስድስት ዘመናዊ መኪኖችን የሽልማት ዕጣዎችን የማውጣት ሥነ-ሥርዓት አከናውኗል፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም በዚህ የሽልማት መርሃ-ግብር ከዚህ ቀደም አራት የኤሌክትሪክ መኪኖችን እንዲሁም 13 ባለሶስት እግር ተሽከርካሪዎችን ለባለ ዕድለኛ ደንበኞቹ ማስረከቡን ገልጿል፡፡ በተጨማሪም 372 ዘመናዊ ስማርት ስልኮችንና የቴሌብር ኤሌክትሮኒክስ ገንዘብን ጨምሮ በሽልማት መርሐ ግብሩ ከ127 ነጥብ 8 ሚሊየን ብር በላይ አጠቃላይ ዋጋ ያላቸውን ሽልማቶች ሰጥቷል። የኢትዮ ቴሌኮም ቺፍ ቴክኖሎጂ ኦፊሰር ታሪኩ ደምሴ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ እውን ለማድረግ የጀመራቸውን ሰፋፊ ስራዎች አጠናክሮ በማጠናከር የበኩሉን ገንቢ ሚና እንደሚወጣ ተናግረዋል፡፡ የኢትዮ 130 ሜጋ ፕሮሞ እና ኢትዮ 131 ላኪ ስሎት ሽልማት ላይ እድለኛ የሆኑት አሸናፊዎች በሽልማቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል፡፡ ካነጋገርናቸው ባለእድለኞች መካከል ከጅማ ከተማ የመጡት ጥንዶች በጅማ ከተማ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሰራተኛ የሆነው ሳሙኤል ጣፋ እና ባለቤቱ ኢሌኒ ለማ ሽልማቱ ድርብ ደስታን እንደፈጠረላቸው ይገልጻሉ፡፡ ሌላው ባለ እድለኛ ገብረ ህይወት ታምር በበኩሉ ኢትዮቴሌኮም የኢትዮ 130 ሜጋ ፕሮሞ እና ኢትዮ 131 ላኪ ስሎት ሽልማት ዕድለኛ በመሆኑ መደሰቱን ተናግሯል፡፡ ኩባንያው በቀጣይም ደንበኞቹን ተሸላሚ የሚያደርገውን ቴሌ ፕለይ የተሰኘ የሽልማት መርሐ ግብሩን እንደሚያስቀጥልም ተገልጿል። በዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የኢትዮ-ቴሌኮም ከፍተኛ አመራሮች፣ የኢትዮጵያ ሎተሪ አገልግሎት ተወካዮች፣ የሚዲያ አጋሮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል።
ኢንስቲትዩቱ ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅና በማበልፀግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት አሳድጓል
Jan 3, 2026 95
ወልቂጤ ፤ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ):-የኢትዮጵያ የባዮ እና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ችግር ፈቺ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ እና በማበልፀግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ የእንሰት መፋቂያና ማቀነባበሪያ ማሸን በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ በሰስየ ቀበሌ ለሚገኙና በማህበር ለተደራጁ አርሶ አደሮች አስረክቧል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ካሳሁን ተስፋዬ እንዳሉት ኢንስቲትዩቱ የማህበረሰቡን ኑሮና የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴ የሚያቀሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን እያፈለቀ እና እያበለጸገ ይገኛል። ከዚህ ቀደምም የአቮካዶ ዘይት መጭመቂያ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለሲዳማ ክልልና ለደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል እንዲሁም የበቆሎ መሸልቀቂያ ማሽን ለምስራቅ ጉራጌ ዞን ተጠቃሚዎች ማስተላለፉን ተናግረዋል። አሁን ላይ ጥራቱን የጠበቀ የእንሰት መፋቂያና ማብላያ ማሽን በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ የሰስየ ቀበሌ በማህበር ለተደራጁ 15 ወጣቶች ማቅረብ ችሏል ነው ያሉት። ማሽኑ የጊዜና የጉልበት ብክነትን በመቀነስ የቆጮ እና ቡላ ማብላያ ሂደትን ከማሳጠር ባለፈ የተሻለ ምርት የሚያስገኝ መሆኑን ገልጸዋል። የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሳይንስ፣ ኢንፎርሜሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሰላሙ አማዶ፣ ከእንሰት ምርት ምግብ በማዘጋጀቱ ሂደት የሴቶች ጫና ይበዛ እንደነበር ጠቅሰው ማሽኑ ወንዶች ጭምር በስራው እንዲሳተፉ የሚያስችል ነው ብለዋል። በዚህ ማሽን ከቆጮና ቡላ ባለፈ ሌሎች ምግቦችን ማዘጋጀት እንደሚቻል አመልክተው፤ ማሽኑ ለብዙዎች የሥራ ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል። ማሽኑን በክልሉ እንሰት አምራች አካባቢዎች ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የእንሰት ሰብል ዝርያን በማሻሻል ምርታማነትን በማሳደግ የአምራቹን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት ይሰራል ያሉት ደግሞ የጉራጌ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ ናቸው። ችግር ፈቺ የሆነ የእንሰት መፋቂያ እና በአጭር ጊዜ ያለ ብክነት ወደ ምርት የሚቀይሩ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ለህብረተሰቡ ተደራሽ እንዲሆኑም አስተዳደሩ ድርሻውን ይወጣል ብለዋል። በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ የሰስየ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አዲሱ ምስጎ፤ የተሰጣቸው ማሽን የእንሰት መፋቂያ፣ የአሚቾ ማድቀቂያ እና የቡላ መጭመቂያ መሆኑን ተናግረዋል። ማሽኑ በቀን አስከ 40 እንሰት መፋቅ የሚያስችል ሲሆን ይህም ተጠቃሚነታቸውን የበለጠ የሚያሳድግ መሆኑን ጠቁመዋል። ወይዘሮ ይስሬሽ ሰክት በበኩላቸው ማሽኑ እንሰት ፍቆ ለምግብነት ለማዋል የሚባክነውን ጊዜ እና ጉልበት የሚቀንስ መሆኑንም አንስተዋል።
የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር አማራጭ ቅንጦት ሳይሆን የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሀገር ሉዓላዊነት የማስከበሪያ መሠረት ነው - ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ
Jan 3, 2026 203
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2017(ኢዜአ)፦ የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር አማራጭ ቅንጦት ሳይሆን የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሀገር ሉዓላዊነት የማስከበሪያ መሠረት መሆኑን የኢፌዴሪ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ገለጹ። “የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረም ልዕልና ለሀገር ሉዓላዊነት” በሚል መሪ ሃሳብ በሀገር አቀፍ ደረጃ የመጀመሪያ የሆነ የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር አውደ ጥናት በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢመደአ) ዋና መስሪያ ቤት ዛሬ ተካሂዷል፡፡ ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በወቅቱ እንደገለጹት፤ ኤሌክትሮኒክ ዋርፌር አማራጭ ቅንጦት ሳይሆን የ21ኛው ክፍለ ዘመን የሀገራት ሉዓላዊነት መሠረት ነው። በዚህ ዘመን የሀገራት ኃይል መገለጫዎች በከፍተኛ ፍጥነት እየተቀያየሩ የመጡበት ወቅት መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም ሀገራት ሉዓላዊነታቸውን ለማስከበር በመሬት፣ በባሕር፣ በአየርና በሕዋ ክልል ውስጥ በሚደረጉ ፍልሚያዎች ብቻ ይጠቀሙ እንደነበረም ገልጸዋል። ዛሬ ዘመናዊ ውጊያ የሚካሄደው በማይታይ እና የጦርነቱን ዕጣ ፈንታ በሚወስን ረቂቅ የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረም ምህዳር ውስጥ መሆኑንም አብራርተዋል። ከዚህ አኳያ የኢትዮጵያ የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረምን መጠቀም የደህንነት ብቻ ሳይሆን የህልውና ጉዳይም ጭምር መሆኑን ገልጸዋል። የሀገራችን ሰፊ የቆዳ ስፋት እና ተለዋዋጭ ቀጣናዊ ጂኦ ፖለቲካዊ ሁኔታ ካለን ተጨባጭ የመከላከል አቅም ጋር መጣጣም ይኖርበታል ሲሉም አስገንዝበዋል፡፡ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ በበኩላቸው፤ የዘመኑ ጂኦ ፖለቲካዊ ፉክክር መልክ እየቀየረ መምጣቱን ገልጸዋል። የሀገር ሉዓላዊነት የሚረጋገጠው በመሬት፣ በባህር፣ በአየር፣ በሕዋ ወይም በሳይበር ላይ በሚደረግ ተጋድሎ ብቻ ያለመሆኑን አመልክተው፤ በማይዳሰስና በረቂቁ የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረም እንደሆነ ጠቅሰዋል። ዛሬ የተዘጋጀው አውደ ጥናት ይህንን የፉክክር ዘርፍ በብቃት ለመረዳትና በስፔክትረሙ ላይ አስተማማኝ የበላይነትን ለመጨበጥ የሚያስችል ብሔራዊ አቅም ለመገንባት መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለሚገጥሟት ዘመናዊ የጸጥታ ስጋቶች የምትሰጠው ምላሽ በሳይንሳዊ ትንታኔ እና በተቋማዊ ቅንጅት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ገልጸው፤ ለዚህም የተቋማት አመራር ቁርጠኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። በየተቋማቱ የሚገኙ እምቅ አቅሞችን መደመርና ቅንጅት መፍጠር ትኩረት እንደተሰጠው አብራርተዋል። የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀኔራል አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት፤ የሀገራት ደህንነት የሚረጋገጠው መረጃን ቀድሞ የማግኘት፣ ስፔክትረሙን የመቆጣጠርና ጠላት እንዳይጠቀምበት የማድረግ የቴክኖሎጂ የበላይነትን በመያዝ ነው። ይህንን ምህዳር የተቆጣጠረ ወገን መረጃን ቀድሞ የማግኘት፣ ውሳኔን በፍጥነት የመወሰንና የድል ልዕልናን የመያዝ ስትራቴጂካዊ ብልጫ እንደሚኖረውም አስረድተዋል። በመድረኩ ላይ የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር ታሪካዊ ዳራ፣ አሁናዊ የሀገራት ተሞክሮ፣ እንዲሁም የኢትዮጵያ ወቅታዊና መጻኢ ሁኔታዎችን የዳሰሰ መነሻ ጽሁፍ በኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ዳንኤል ጉታ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል፡፡ በአውደ ጥናቱ ላይ የተለያዩ ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች የተገኙ ሲሆን፤ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ፣ የኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ፣ በመከላከያ መረጃ ዋና መምሪያ የኤሌክትሮኒክ ዋርፌር መምሪያ ኃላፊ ኮሎኔል ዶክተር አሸናፊ ኦሊ፣ እንዲሁም የመከላከያ ኢንጂነሪንግ ኢንዱስትሪ ግሩፕ ኃላፊ አቶ ጌታቸው ኃይለማርያም በፓናሊስትነት ተሳትፈዋል፡፡ በፓናል ውይይቱ በዋናነት የኤሌክትሮ ማግኔቲክ ስፔክትረምን በአግባቡ በመቆጣጠርና በመምራት የኢትዮጵያን አሁናዊና መጻኢ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ዘርፉን የሚመራ ተቋም መገንባት፣ በዘርፉ የሚካሄዱ ጥናትና ምርምሮችን ማላቅ፣ እንዲሁም በባለድርሻ ተቋማት መካከል ያለውን ትብብርና ቅንጅት ይበልጥ ማሳደግ እንደሚያስፈልግ ተመላክቷል፡፡
የግብይት ሥርዓቱን ዲጂታላይዝ ለማድረግ የተጀመሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው
Jan 3, 2026 116
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ)፦ የግብይት ሥርዓቱን ዲጂታላይዝ ለማድረግ የተጀመሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። በሚኒስትሩ የተመራ የልዑክ ቡድን በከተማዋ ተዘዋውሮ የንግድ እንቅስቃሴ ቅኝት አድርጓል። በዚሁ ጊዜ ተቋማቸው በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የተያዙ ግቦች እንዲሳኩ የድርሻውን እየተወጣ ነው ብለዋል። የወጪ ንግድ ኮንትራትና የፍቃድ አሰጣጡን ሙሉ ለሙሉ በዲጂታል ሥርዓት መቀየሩን ገልጸው፣ የዲጂታል ግብይት እንዲሳለጥም ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ለአብነትም በአንድ ወር ብቻ ጤፍ በዘመን ገበያ የ53 ሚሊዮን ብር ግብይት መፈጸሙን አንስተዋል። መንግስት የዲጂታል ግብይትን ለማሳለጥ በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ወደ ዲጂታል ግብይት እንዲገቡ ይደረጋል ብለዋል። እንደ ሚኒስትሩ ማብራሪያ በቁም እንሰሳት ንግድ ላይ የደላላ ጣልቃገብነት በመቀነስና አሰራሩን በማዘመን የተሻለ አፈጻጸም ተመዝግቧል። የቁም እንስሳት የግብይት ማዕከላትን በማስፋት የግብይቱን ሥርዓት ግልጽና ዘመናዊ መደረጉን ገልጸው፤ከቁም እንስሳት ወጪ ንግዱ ገቢ እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በ2018 በጀት ዓመት ስድስት ወራት ከቁም እንስሳት ወጪ ንግድ ከ30 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱንም ነው የተናገሩት። በ2018 በጀት ዓመት ከቁም እንስሳት ወጪ ንግድ 70 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት ታቅዷል።
በክልሉ በዲጂታል አሰራር የተደገፉ አገልግሎቶችን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
Jan 3, 2026 75
አርባ ምንጭ፤ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በዲጂታል አሰራር የተደገፉ አገልግሎቶችን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት መደረጉ ተገለጸ፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የስራ አፈጻጸም ግምገማ በአርባ ምንጭ ከተማ ዛሬ ተካሄዷል። በመድረኩ ላይ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የስራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) በክልሉ ዲጂታል 2030ን በማሳካት የህዝቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሠራ ይገኛል። ''ከዲጂታል ቴክኖሎጂ ውጭ የሚታሰብ መንግስታዊ አገልግሎት አይኖርም'' ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ፥ ወረቀት አልባ አገልግሎቶችን በማስፋፋት ህዝቡን ከእንግልትና ከአላስፈላጊ ወጪ ለማዳን በትኩረት ይሰራል ብለዋል። ከሁሉም በላይ በክልሉ በዲጂታል አሰራር የተደገፉ አገልግሎቶችን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቷል ነው ያሉት። የፋይዳ መታወቂያ ዜጎችን ከተለያዩ አገልግሎቶች ጋር በማስተሳሰር ህይወትን በእጅጉ የሚያቀል በመሆኑ ዜጎች የዚሁ ትሩፋት ተጠቃሚ ለመሆን ፋይዳ መታወቂያ መያዝ እንዳለባቸውም ገልጸዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ ቦጋለ ቦሼ (ዶ/ር) የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን ለማሳካት በተደረጉ ጥረቶች ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት መከናወናቸውን አስረድተዋል፡፡ በክልሉ የተጀመሩ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እና የዲጂታል መታወቂያ ስራዎች ጉልህ ፋይዳ አላቸው ብለዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ዕቅድ ለማሳካት ክልሉ ድርሻውን እንዲጫወት ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እንደሚሠራም ጠቁመዋል። በመድረኩ የክልልና የዞኖች እንዲሁም የከተማ አስተዳደሮች ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ታድመዋል።
በከተሞች ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ የዲጂታል አገልግሎቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jan 3, 2026 68
ሆሳዕና ፤ ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ) ፡- በከተሞች ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ የዲጂታል አገልግሎቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተመላከተ፡፡ የቢሮ ኃላፊዎቹ እንደገለፁት፤ በከተሞች ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመሩ የዲጂታል አገልግሎቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ ለኢዜአ እንዳሉት በክልሉ ከተሞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ በማደራጀት ለተገልጋዩ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እየተሰራ ነው፡፡ የመደመር መንግሥት እይታን በመተግበር ዜጎች ባሉበት ሆነው በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ ለማስቻል ስማርት ከተሞችን መፍጠር ላይ ትኩረት መሰጠቱን ጠቁመዋል፡፡ በዚህም በክልሉ ዘጠኝ ከተሞች የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎትን ዲጂታላይዝድ በማድረግ ፈጣንና ከብልሹ አሰራር የጸዳ አገልግሎት እየተሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በቀጣይም ተግባሩን በማስፋት በ15 ከተሞች ለማስጀመር ቅድመ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የሲዳማ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብሩክ ሰለሞን በበኩላቸው በከተሞች ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ይነሱ የነበሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ተግባራዊ መደረጉን አንስተዋል። በተለይም የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ብልሹ አሰራሮችን ለማረምና የተገልጋይ እርካታን ለመጨመር መሰራቱን ጠቁመዋል፡፡ አገልግሎቱን ለማስፋትም የመቶ ቀናት እቅድ መዘጋጀቱንም ጠቁመዋል፡፡ በክልሉ የመንግሥት አገልግሎትን የተቀላጠፈ ለማድረግ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በሰመራ ከተማ መጀመሩን የገለፁት ደግሞ የአፋር ክልል ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኢንጂነር ጎቦኦ መሀመድ ናቸው። በዚህም ቀደም ሲል በከተማ አገልግሎት አሰጣጥ የነበሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቀነስ መቻሉን አንስተዋል። አገልግሎቱን በማስፋትም በክልሉ አዋሽን ጨምሮ በሌሎች ከተሞች ተደራሽ በማድረግ ተገልጋዩን ለማርካት መታቀዱን ገልፀዋል፡፡ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በበኩላቸው መንግሥት በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ሪፎርሞች መተግበሩን ተናግረዋል፡፡ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥ መዘመንም የማህበረሰቡን እንግልት ለመቅረፍ የተጀመረዉ ጥረት አካል መሆኑን ጠቁመዋል። ለዚህም በዲጂታል የታገዘ አገልግሎትን እስከ ቀበሌ መዋቅር በማስፋት በዘርፉ የሚነሱ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ አመራሩ ትኩረት ሰጥቶ ሊሰራ እንደሚገባም ሚኒስትሯ አሳስበዋል፡፡ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር የገጠር ትራንስፎርሜሽንን መሰረት ያደረገ ሀገራዊ የንቅናቄ መድረክ በሆሳዕና ከተማ ማካሄዱን መዘገባችን ይታወሳል።
የአብርሆት ቤተ-መጻሕፍትን ወደ ላቀ የዲጂታል ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ሦስት ታላላቅ የቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶች ይፋ ሆኑ
Jan 3, 2026 100
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ)፦የአብርሆት ቤተ-መጻሕፍትን ወደ ላቀ የዲጂታል ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ሦስት ታላላቅ የቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶች ዛሬ በይፋ የማስጀመር ተግባር ተከናውኗል። ይህንንም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት በመገኘት የቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶችን ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። ከንቲባ አዳነች፥ አቤቤ የአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት በመዲናዋ የንባብና የምርምር ባህል ማዕከል ሆኖ ስራ ከጀመረ አራት ዓመታት መቆጠራቸውን ገልጸዋል። ዛሬ በቤተ-መጻሕፍቱ በመገኘትም፥ ተቋሙን ወደ ላቀ የዲጂታል ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ሦስት ታላላቅ የቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶችን በይፋ ማስጀመራቸውን ጠቁመዋል። በዓመት በአማካይ ለ1 ነጥብ 8 ሚሊዮን አንባቢዎች አገልግሎት እየሰጠ የሚገኘውን ይህንን ተቋም ይበልጥ ለማዘመን የሚያስችሉ፦ የተቀናጀ የቤተ-መጻሕፍት አስተዳደር ሥርዓት፣ ዘመናዊ የዲጂታል ቤተ-መጻሕፍት እና ዓለም አቀፍ የምርምር መድረክ (Research Portal) በይፋ ሥራ እንዲጀምሩ መደረጉን አመልክተዋል። አገልግሎቶቹ አብርሆት በአዲስ አበባ ብቻ የተገደበ እንዳይሆን ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥሩ የተናገሩት ከንቲባዋ ማንኛውም ተማሪም ሆነ ተመራማሪ በየትኛውም የኢትዮጵያ አካባቢ ሆኖ የአብርሆትን የዕውቀት ማዕድ መቋደስ እንዲችል ያደርጋሉ ነው ያሉት። በተጨማሪም የታሪክ ሰነዶችን በዲጂታል መንገድ ተጠብቀው ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፉ ትልቅ እገዛ እንደሚኖራቸውም አክለዋል። ከንቲባዋ ቴክኖሎጂዎቹን በማልማት አስተዋጽኦ ላበረከቱ ባለድርሻ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
የስማርት አዳማ ፕሮጀክት ግቦችን ለማሳካት ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቷል
Jan 2, 2026 181
አዳማ፤ ታህሳስ 24/2018(ኢዜአ)፦ የስማርት አዳማ ፕሮጀክት ግቦችን ለማሳካት ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ማስፋፋት ላይ ትኩረት መሰጠቱን የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ ገለፁ። በአዳማ ከተማ ዲጂታል መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማጠናክርና ህብረተሰቡን የፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ ያለመ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ በወቅቱ እንደገለፁት የስማርት አዳማ ፕሮጀክትን ለማሳካት የሚደረገው ጥረት አካል የሆነው ፋይዳ መታወቂያ አገልግሎት ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቷል። ይህም የከተማዋን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶች ዲጂታላይዝድ በማድረግ ህብረተሰቡ ባለበት ቦታ ሆኖ የመንግስት አገልግሎትን በተቀላጠፈና አስተማማኝ በሆነ መንገድ ለማግኘት ያግዛል ብለዋል። የመንግስት አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝድ ማድረግ ተገልጋዩ ከመሬት ሀብት አስተዳደርና አጠቃቀም ጋር የሚያነሳቸው ጥያቄዎችን፣ የገቢ ግብር፣ የትራንስፖርት አገልግሎትና የከተማዋን ፀጥታ በካሜራ በመቆጣጥር ምላሽ መስጠት እንደሚያስችል ጠቁመዋል። የስማርት ሲቲ አካል የሆነው የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሁሉንም አገልግሎቶች ዲጂታላይዝድ በማድረግ በአንድ ቦታ ለማግኘት የጎላ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ብለዋል። የዲጂታል ቴክኖሎጂው ስርአትም ሌብነትና የመሬት ምዝበራን በማስቀረት የከተማዋን ገቢ በማሳደግ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማቶች እንዲሳለጡ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። በውይይቱ ከተሳተፉ የአዳማ ከተማ ነዋሪ ሀሰን ጂማ እንደገለፁት የከተማዋ የዲጂታል አገልግሎት ጊዜና ገንዘባቸውን ቆጥቦላቸዋል። ዲጂታል አገልግሎቱ ከፋይዳ መታወቂያ ጋር መተሳሰሩ ቀደም ሲል በከተማዋ ይስተዋሉ የነበሩ ብልሹ አሰራሮችን በመቅረፍ የተሻለ አገልግሎት እንድናገኝ የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ በላቸው ደምሴ ናቸው።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት ነው
Jan 2, 2026 106
ወልዲያ፤ ታህሳስ 24/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት መሆኑን የኢንፎርሜሽ ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ታኅሣሥ 11 ቀን 2018 ዓ.ም የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ስትራቴጂ ይፋ በማድረግ የዲጂታል 2025 ክንውን ደግሞ በስኬት መጠናቀቁን መግለፃቸው ይታወሳል። በሰሜን ወሎ ዞን ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂና የኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 በዘርፉ የሚታይና የሚጨበጥ ውጤት የመጣበት መሆኑን ገልጸዋል። የአይሲቲ ባለሙያ የሆኑት ታደሰ አብዬ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በዘርፉ ጽኑ መሰረት ያኖረ ስኬታማ ስራ መሆኑን ተናግረዋል። የስትራቴጂው መተግበር በበርካታ ተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥና የአሰራር ቅልጥፍናን፣ የቁጥጥርና ተጠያቂነት አሰራርን በማስፈን እንዲሁም ብልሹ አሰራርን መከላከል አስችሏል ብለዋል። ይህም ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በማሳካት የአገራችንን ሁለንተናዊ እድገት ዳር ለማድረስ መሰረት የጣለ በመሆኑ በጋራ ልንረባረብ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። የኮሙኒኬሽን ባለሙያው አሰፋ መስፍን፤ በኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት እመርታዊ ለውጥና ማንሰራራት ማምጣቱን ገልጸው ለቀጣዩ እቅድ የላቀ ስኬት መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። በተለይም በአርተፊሻል ኢንተለጀንስና ሌሎች የቴክኖሎጂ ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶችን አንስተው በፋይናንስ ተቋማትና ሌሎች ተቋማት የታየውን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማሳያነት ጠቅሰዋል። በመሆኑም የዲጂታል ልማት ስትራቴጂ ለፍጥነት፣ ፈጠራና ለሀገር እድገት ወሳኝ በመሆኑ ለ2030 ስትራቴጂክ እቅድ ስኬት ሁላችንም የድርሻችንን መወጣት አለብን ብለዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስኬቶች ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 መሠረት ናቸው
Jan 2, 2026 103
ጅግጅጋ፤ ታህሳስ 24/2018(ኢዜአ)፦ በአገልግሎት አሰጣጥና በዜጎች ላይ መሰረታዊ ለውጥ ያመጣው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ ስኬቶች ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 መሰረት መሆናቸውን በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉ ባለሙያ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ማጠናቀቅያ እና በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት ላይ ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ መቶ በመቶ በሚባል ደረጃ የተሳካ መሆኑን መግለጻቸው ይታወሳል ። በስትራቴጂው በግብርና፣ በማዕድን ብሎም በኢንዱስትሪው እንደተገኘው ስኬት በዲጂታሉ ዘርፍም መገኘቱን አንስተው ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስኬት ፅኑ መሰረት እንደሚሆነው ማመላከታቸውም እንዲሁ። በዚሁ ጉዳይ ላይ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ የአይ ሲ ቲ ዳይሬክቶሬት የኔትወርክ ቡድን መሪ ታደለ ነጋ፤ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የሀገርን ሁለንተናዊ ልማትና እድገትን ለማሳካት ጠንካራ መሰረት ያኖረ መሆኑን ገልጸዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ትግበራ በተቋማት እና በአገልግሎት አሠጣጥ ዘርፈ ብዙ ስኬቶች የተመዘገበበት መሆኑንም አክለዋል። በተለይም የተቋማት የአሠራር ሥርዓት እና ለዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ ለውጦች የተገኙበት መሆኑን ተናግረዋል። በክፍያ ሥርዓት፣ በትምህርት፣ በጤና፣ በግብርናና በሌሎችም ሴክተሮች በዲጂታል ዘርፉ በተሠሩ ሥራዎች አበረታች ስኬቶች መገኘታቸውን ገልጸዋል። ዜጎች የተለያዩ ወጪዎችን የእጅ ስልካቸውን ተጠቅመው በቀላሉ ክፍያዎችን መፈጸም የሚያስችሉ የሲስተም ሥርዓቶች መዘርጋታቸውን ጠቅሰዋል። በጤና ተቋማት ከወረቀት ንክኪ ነጻ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን ገልጸው ይህም የዜጎችን የጤና መረጃዎች ወደ ዲጂታል ሲስተም በማስገባት እና ጤናቸውን ለመጠበቅ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው አንስተዋል። በትምህርት ዘርፉም አገር አቀፍ የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና በበይነመረብ መስጠት መቻሉን ገልፀው ይህም ኩረጃን ማስቀረቱንና ተማሪዎች የተለያዩ ዕድሎችን መጠቀም እንዲችሉ የዲጂታል ማጎልበት ኢንሼቲቭ ተግባራዊ መደረጉን ገልጸዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት በዘርፉ የተገኙት ስኬቶችን መሠረተ በማድረግ ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ውጤታማነት የዘርፉ ባለሙያዎች ድጋፍ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።
ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የወንጀል መከላከልና ምርመራ ሥራን ወደ ላቀ የቴክኖሎጂ ምዕራፍ በሚያሸጋገር መልኩ ይተገበራል
Jan 2, 2026 104
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 የወንጀል መከላከልና ምርመራ ሥራን ወደ ላቀ የቴክኖሎጂ ምዕራፍ በሚያሸጋገር መልኩ እንደሚተገበር የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት፤ ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል ዕድል መፍጠር፣ በዜጎችና ተቋማት መካከል መተማመንን ማጎልበት የስትራቴጂው ቁልፍ ትልሞች መሆናቸውን መግለጻቸው ይታወቃል። የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ለወንጀል መከላከልና ምርመራ ሥራዎች ቴክኖሎጂን በስፋት እየተጠቀመ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የተለያዩ መተግበሪያዎችን በራስ አቅም በማበልጸግ እንዲሁም ከአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ እና ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በፖሊስ ሥራዎች ላይ ለውጥ እንዲመዘገብ ማስቻሉንም ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅት ሕብረተሰቡ የወንጀል ጥቆማዎችንና የሚፈልጋቸውን መረጃዎች በአካል ፖሊስ ጣቢያ ሳይገኝ በሞባይል ስልኩ ብቻ የሚያገኝበት ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ኮሚሽነር ጄኔራሉ ገልጸዋል። አክለውም ከአንድ ወር በኋላ ሰው አልባ የፖሊስ ጣቢያ (Smart Police Station) በአዲስ አበባ ሥራ እንደሚጀምር ጠቁመዋል። የጣት አሻራን አውቶሜት የማድረግ ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቁመው፤ የጦር መሣሪያ ምዝገባን ከፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር ቁጥጥር የሚደረግበት ሥርዓት መዘርጋቱንም ጠቅሰዋል። ፌደራል ፖሊስ በ2030 የወንጀል ምርመራ፣ መከላከልና የውስጥ አሠራሮችን በቴክኖሎጂ ሙሉ በሙሉ ለማዘመን በቁርጠኝነት እየሠራ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም ፖሊሳዊ አገልግሎቶችን በላቀ ደረጃ የሚያጎለብት መሆኑን አስረድተዋል። በቀጣይም 196 ሀገራት የሚሳተፉበት የዓለም አቀፉ ፖሊስ (ኢንተርፖል) ጉባኤ በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ጠቁመው፤ ተቋሙ በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና የዘመነ መሆኑን ለማሳየት በትኩረት እየተሠራ መሆኑን አረጋግጠዋል።
ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መሳካት ዘመኑን የዋጁ የሥልጠና ፕሮግራሞች እየተከፈቱ ነው
Jan 2, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መሳካት በዘርፉ ብቁ ባለሙያ ለማፍራት ዘመኑን የዋጁ የሥልጠና ፕሮግራሞች እየተከፈቱ መሆኑ ተገለጸ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ባስጀመሩበት ወቅት፤ ስትራቴጂው ተደራሽ፣ ፍትሐዊ እና አስተማማኝ የዲጂታል ምኅዳር መፍጠር ላይ ማተኮሩን ገልጸዋል። የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በቴክኒክና ሙያ መስክ አበረታች ለውጥ እንዲመዘገብ ዐቅም ፈጥሯል። ለአብነትም ስትራቴጂው ኢንስቲትዩቱ የአሰለጣጠን ሂደቱን ዘመኑን በዋጀ መልኩ እንዲቃኝና የሰዎችን የዲጂታላይዜሽን ግንዛቤ እንዲጎለብት መሰረት መጣሉን አንስተዋል። ኢንስቲትዩቱ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ሊያሳካቸው ከያዛቸው ዓላማዎች ጋር በማስተሳሰር ለመተግበር የሚያስችለውን የሠነድ ዝግጅት እያደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂክ ግቦችን ለማሳካት የተሻለ የዲጂታል ክኅሎት ያላቸው ሰልጣኞችን ማፍራት በትኩረት የሚሠራበት ጉዳይ መሆኑን አመላክተዋል። አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ፣ የሳይበር ሴክዩሪቲና ሌሎች የሥልጠና ዓይነቶች ለስትራቴጂው መሳካት ሚናቸው የላቀ መሆኑን ለአብነት አንስተዋል። በተጨማሪም በዲጂታል ክኅሎት የበለጸገ ባለሙያ ለማፍራትና የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በተሻለ መንገድ ለማበልጸግ ተቋሙ ራሱን በግብዓትና በአደረጃጀት እያጠናከረ እንደሚገኝም ነው ያስታወቁት።
ባህላዊ እሴቶችን በጥናት በማስደገፍ ለጋራ ትርክት ግንባታ ለማዋል በቅንጅት እየተሰራ ነው
Jan 1, 2026 337
አምቦ ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦ ባህላዊ እሴቶችን በጥናት በማስደገፍ ለጋራ ትርክት ግንባታ ለማዋል በቅንጅት እየሰራ መሆኑን የኦሮሞ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት አስታወቀ። በሀገር በቀልና ኪነጥበብ ላይ ያተኮረ ኮንፍረንስ በአምቦ ዩኒቨርሲቲ ተካሂዷል፡፡ የኦሮሞ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት ምክትል ዳይሬክተር አቶ ዝናቡ አስራት በወቅቱ እንዳሉት ኢንስቲትዩቱ የኦሮሞ ህዝብ ታሪክና ባህል እሴቶችን በጥናት በማስደገፍ ለጋራ ትርክት ግንባታ ለማዋል እየሰራ ነው፡፡ የመደጋገፍ የባህል እሴቶችን በጥናትና ምርምር በማስደገፍ ለትውልድ ለማስተላለፍና ይበልጥ ለማስተዋወቅ ከሌሎች ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በቅንጅት መስራታቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ የባህል እሴቶቹ ለትውልድ እንዲተላለፉና በትምህርት ስርአት ውስጥ እንዲካተቱ እንዲሁም በመጽሃፍት እንዲታተሙ ምክረሀሳብ መቅረቡን ተናግረዋል፡፡ በጥናትና ምርምር ተደግፈው የተጻፉ የህትመት ውጤቶችም ለህብረተሰቡ እንዲደርሱ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ የሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን የጥናትና ምርምር ማእከል ዳይሬክተር ሳሙኤል ሌይኩን (ዶ/ር) ፤ ለአራተኛ ጊዜ በተካሄደው በሀገር በቀል የኪነጥበብ ኮንፍረንስ ላይ የኦሮሞን ህዝብ የመተጋገዝ ባህል በኪነጥበብ ስራዎች ላይ የተቃኙበትን አውድ የሚያስረዳ ጥናት ይዘው መቅረባቸውን ተናግረዋል። የምርምር ውጤቶች ትውልዱ ባህላዊ እሴቱን በመረዳት ባህሉንና ቋንቋውን እንዲያዳብር ትልቅ አስተዋጽኦ አላቸው ብለዋል፡፡ የአምቦ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ባይሳ ለታ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው ሀገር በቀል የባህል እሴቶችን በማጥናት ለህብረተሰብ ግንባታ የሚውሉበትን ሂደት ለማሳለጥ ከኪነ ጥበብ ስራዎች ጋር ለማስተሳሰር መሰራቱን ተናግረዋል፡፡ ባህልን ከኪነ ጥበብ ስራዎች ጋር ማቀናጀት በሀገራዊ እድገት ውስጥ ትልቁን ሚና የሚጫወት በመሆኑ የኮንፍረንሱ መካሄድ ይህን ለማሳካት ልምድ የሚወሰድበት ጭምር መሆኑን ጠቁመዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ መምህርና ተመራማሪ ፕሮፌሰር ተሰማ ታአ፤ የባህልና የታሪክ እሴቶችን በማጥናት ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማዋል መሰረታዊ ጉዳይ ነው ብለዋል። ባህላዊ እሴቶችን ለትውልድ ለማስተላለፍም መሰል የባህል የምርምር ኮንፍረንሶች ተጨማሪ አቅም መሆናቸውን አስረድተዋል። የኦሮሞ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት ከአምቦ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ባዘጋጀው ኮንፍረንስ ላይ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ ተመራማሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፈዋል፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ የጥናትና ምርምር ሥራዎች ማከናወኑን አጠናክሮ ይቀጥላል
Jan 1, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ የጥናትና ምርምር ሥራዎች ማከናወኑን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጸ፡፡ ዩኒቨርሲቲው የተመሠረተበትን 75ኛ ዓመት የአልማዝ ኢዮቤልዩ በዓል አስመልክቶ የተቋሙን አጠቃላይ ሀገራዊ አበርክቶ የሚዳስሱ ጥናታዊ ጽሑፎች የቀረቡበት ሲምፖዚየም ተካሂዷል። ዩኒቨርሲቲው ባለፉት 75 ዓመታት በሀገሪቷ የሰው ኃይል ልማት፣ በጤና፣ በፖለቲካ፣ በማኅበራዊና በኢኮኖሚ ዘርፎች ለሀገር ያበረከተውን አስተዋጽኦ የተመለከቱ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበዋል፡፡ የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ጄይሉ ዑመር (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ዩኒቨርሲቲው ለሀገር ዕድገት ወሳኝ ሚና የተጫወቱ ምሁራን ያፈራ አንጋፋ ተቋም ነው ብለዋል። ተቋሙ በቀጣይም ጥራት ያለው የሰው ኃይል ለማፍራትና ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ የምርምር ሥራዎችን ለማከናወን ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማኅበራዊና ኢኮኖሚ ምርምር ተቋም ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ዓለሙ መኮንን በሲምፖዚየሙ ላይ ባቀረቡት ጽሑፍ፤ ዩኒቨርሲቲው ባለፉት አሥርተ ዓመታት በሀገሪቷ የሥራ መስኮች የተሰማሩ ብቁ ባለሙያዎችን በማፍራት ረገድ ግንባር ቀደም መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር የሚራመድ የሰው ኃይል በማፍራት ረገድ ጠንካራ ሥራ ሊሠራ እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡ የታሪክ ምሁሩ ደቻሳ አበበ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ተቋሙ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ በማስተዋወቅ ረገድ ያለበትን ኃላፊነት ሊወጣ እንደሚገባ አመልክተዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ 32 ሚሊዮን ማሳዎች በዲጂታል የመረጃ ሥርዓት ተደራጅተዋል
Jan 1, 2026 108
አርባ ምንጭ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦በሀገር አቀፍ ደረጃ 32 ሚሊዮን ማሳዎች በዲጂታል የመረጃ ሥርዓት መደራጀታቸውን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የገጠር መሬት አስተዳደር ሥርአትን ከፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ጋር ለማስተሳሰር ያለመ ክልል አቀፍ የንቅናቄ መድረክ ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የግብርና ሚኒስቴር የገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ትዕግስቱ ገብረመስቀል እንዳሉት፣ የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ የሚያግዙ የግብርና መረጃዎችን እንደ የአፈር መረጃ፣ የአየር ፀባይ ሁኔታ፣ የማዳበሪያ አቅርቦት እና የመሬት መጠቀሚያ ስርአት አገልግሎትን ዲጂታላይዝድ ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ ነው። ይህም ግብርናውን ለማዘመንና የአርሶና አርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚያግዝ ገልጸዋል። ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያም የግብርና መረጃዎችን ዲጂታላይዝድ በማድረግ የአርሶና የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያግዝ ነው ብለዋል። አርሶና አርብቶ አደሮች የመሬት ይዞታቸውን ዲጂታላይዝድ ለማድረግ በተደረገው ጥረት በእስካሁኑ ሂደት በሀገር አቀፍ ደረጃ 32 ሚሊዮን ማሳዎች በዲጂታል ስርአት እንዲደራጁ መደረጉንም አቶ ትዕግስቱ ገልጸዋል። በተለይም አርሶና አርብቶ አደሮች የመሬት ይዞታቸውን በአግባቡ ለማስተዳደር እንዲችሉና ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ ከፋይናንስ አገልግሎት ጋር ማስተሳስር አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው፣ ለዚህም ዲጂታል የፋይዳ መታወቂያ ያግዛቸዋል ብለዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መሬት አስተዳደር ቢሮ ሃላፊ አቶ ሰብስቤ ቡናቤ፤ በክልሉ የአርሶና አርብቶ አደሩን የመሬት አስተዳደር ወደ ዲጂታል ስርአት በማስገባት ተጠቃሚነቱን ለማላቅ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። የክልሉ አርሶና አርብቶ አደሮች የዲጂታል መሬት አስተዳደር ስርአቱ ተጠቃሚ ለመሆንም የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ሊኖራቸው እንደሚገባ አመልክተዋል። የመሬት አስተዳደር ስርአትን ለማዘመን በተደረገ ጥረት በ869 ሺህ 211 አባወራና እማወራዎች እጅ ያለ ከ2 ሚሊዮን በላይ መሬቶች በዲጂታል ስርአት እንዲደራጅ መደረጉንም ገልጸዋል። ይህን አጠናክሮ ለመቀጠልም በሚቀጥሉት አንድ መቶ ቀናት በክልሉ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን አርሶና አርብቶ አደሮች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተናግረዋል። ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ አገልግሎቶችን በማቀላጠፍ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት እያገዘ ነው ያሉት ደግሞ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የምዝገባ አስተባባሪ ደጀኔ ገብሬ ናቸው። ዲጂታል መታወቂያ ለአርሶና አርብቶ አደሮች የብድር አገልግሎቶችን በማግኘት በስራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ያስችላል ብለዋል። ለአንድ ቀን በተዘጋጀው የንቅናቄ መድረክ ላይ የፌደራል፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ የዞኖችና የወረዳ አመራሮች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።