ቀጥታ፡
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ኢትዮጵያ እና አዘርባጃን በሰው ሰራሽ አስተውሎት ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር ቁርጠኛ ናቸው - ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር)
Feb 28, 2026 70
አዲስ አበባ፤ የካቲት 21/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና አዘርባጃን በሰው ሰራሽ አስተውሎት ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር እና የልምድ ልውውጥ ለማድረግ ጠንካራ ፍላጎት እንዳላቸው የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ወርቁ ጋቸና(ዶ/ር) በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተመራው የኢትዮጵያ ልዑክ በአዘርባጃን ያደረገውን ይፋዊ የስራ ጉብኝት አስመልክተው ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እና ልዑካቸው የአዘርባጃን አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት አካዳሚን መጎብኘቱን ገልጸዋል። አካዳሚው በአንድ ዓመት ከስድስት ወር ጊዜ ውስጥ የትምህርቱ ዘርፍን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች የሰው ሰራሽ አስተውሎት ተደራሽነት በማስፋት ረገድ ውጤታማ ስራ ማከናወኑን ከጉብኝቱ መረዳት መቻሉን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ከስድስት ዓመታት በፊት መቋቋሙንና ውጤታማ ተግባራት እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በጉብኝቱ ወቅት በምርምር እና ዳታ ልውውጥ ላይ በትብብር ለመስራት በሀገራቱ መካከል መግባባት ላይ መደረሱን ነው የተናገሩት። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እና ልዑካቸው የአዘርባጃን የሕዝብ አገልግሎት እና ማኅበራዊ ፈጠራ የመንግሥት ኤጀንሲ(ASAN) የፈጠራ ማዕከልን ጎብኝቷል። አሳን የሚሰጠው አገልግሎት ከአንድ መሶብ አገልግሎት ጋር ተመሳሳይነት ያለው መሆኑን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ በተለይም አገልግሎት አሰጣጡ በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዘ መሆኑ ተሞክሮ የሚወሰድበት ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ ያለውን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በሰው ሰራሽ አስተውሎት እንዲታገዝና ጥራቱ እንዲያድግ በቀጣይ በትኩረት እንደሚሰራ አመልክተዋል። የሁለቱ ሀገራት መሪዎች በውይይታቸው በሰው ሰራሽ አስተውሎትና ዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ በትብብር ለመስራት ከስምምነት ላይ መድረሳቸውን ጠቁመዋል። ሀገራቱ በዘርፉ ልምድ ለመለዋወጥ ፍላጎት እንዳላቸውም ነው የተናገሩት። አጠቃላይ ጉብኝቱ ኢትዮጵያ በቅርቡ ወደ ትግበራ ለገባው ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ እና ለዘርፉ ስራዎች አጋዥ አቅም እንደሚሆን ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።
በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገኙ እምቅ ሃብቶችን በሳይንሳዊ ጥናትና ምርምር በማገዝ የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ መስራት ይገባል
Feb 28, 2026 109
ዲመካ፤ የካቲት 21/2018(ኢዜአ)፡- በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገኙ እምቅ ሃብቶችን በሳይንሳዊ ጥናትና ምርምር በማገዝ የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ መስራት እንደሚገባ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ተናገሩ። የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ እና የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ አገኘሁ ተሻገር፤ በደቡብ ኦሞ ዞን ዲመካ ከተማ በጂንካ ዩኒቨርሲቲ ለሚገነባው የአርብቶ እና ከፊል አርብቶ አደር የምርምር ኢንስቲትዩት የመሰረተ ድንጋይ አኑረዋል። ዩኒቨርሲቲው የማዕከሉን ግንባታ በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጠናቀቅ የምርምር ስራውን መጀመር ይጠበቅበታል ያሉት አፈ ጉባኤው ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በመጠቀም በየአካባቢው ያሉ እምቅ ሀብቶችን በሳይንሳዊ ምርምር በማስደገፍ የላቀ ጥቅም እንዲሰጡ ማድረግ ይገባል ብለዋል። የምርምር ማዕከሉ የዩኒቨርሲቲው ተመራማሪዎች ብቻ የሚጠቀሙበት ሳይሆን በሀገር ውስጥ እና በተለያዩ የዓለም ሀገራት የሚገኙ ተመራማሪዎች የሚሳተፉበትና ልምድ የሚለዋወጡበት እንደሚሆን ገልጸዋል። የምርምር ማዕከሉ በተያዘለት ጊዜ በጥራትና በፍጥነት ተጠናቆ ለሚፈለገው ዓላማ እንዲውል አስፈላጊው እገዛ ድጋፍና ክትትል የሚደረግ ይሆናል ብለዋል። የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዮሐንስ ይትባረክ (ዶ/ር)፤ የሚገነባው የምርምር ማእከል በዋነኝነት አራት መሰረታዊ ተልዕኮዎችን ለመፈፀም የሚያስችል ይሆናል ሲሉ አስረድተዋል። በአካባቢው የግብርና ሥራ እና የእንስሳት ሀብት በሳይንሳዊ የጥናትና ምርምር በማሳደግ የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ አንዱ ሲሆን የቱሪዝም ሀብትን በምርምር በማገዝ ዓለም አቀፋዊ እውቅና እንዲያገኝ ማድረግም ሌላው መሆኑን አንስተዋል። በአካባቢው ያሉ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን የመሰነድ፣ የማስተዋወቅ እና የማሳደግ ተልእኮን ለማሳካትም ወሳኝ ሚና ይኖረዋል ነው ያሉት።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአዘርባጃን የሕዝብ አገልግሎት እና ማኅበራዊ ፈጠራ የመንግሥት ኤጀንሲን ጎበኙ 
Feb 27, 2026 97
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ልዑካቸው የአዘርባጃን የሕዝብ አገልግሎት እና ማኅበራዊ ፈጠራ የመንግሥት ኤጀንሲ (ASAN) የፈጠራ ማዕከልን ጎብኝተዋል።   ጉብኝቱ አዘርባጃን በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) የሚመራ አስተዳደርን ለማስፋፋት እና የሕዝብ አገልግሎቶችን በዲጂታል ለማዘመን የምትከተለውን ስትራቴጂያዊ አካሄድ የሚያሳይ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በሀገሪቱ የAI ኢንጂነሪንግ እና የአመራር ሥልጠና ዋና ማዕከል የሆነውን የAI አካዳሚን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።   ‎ልዑኩ ጉብኝቱን በመቀጠል በክልሉ ውስጥ ካሉ ትላልቅ የነዳጅ እና የጋዝ ማቀነባበሪያ ማዕከላት አንዱ ወደሆነው ሳንጋቻል ተርሚናል እና ወደ አላት ነፃ የኢኮኖሚ ቀጣና አምርቷል።   ጉብኝቶቹ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የንግድ፣ የኢነርጂ እና የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ትብብር ይበልጥ የማጠናከር አቅም እንዳላቸው ጽህፈት ቤቱ ገልጿል።
የኢትዮጵያን የዲጂታል ኢኮኖሚ ለማሳለጥ ወጣቶችን በቴክኖሎጂ የማብቃት ስራ ትኩረት ተሰጥቶታል
Feb 27, 2026 100
አምቦ፤ የካቲት 20/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያን የዲጂታል ኢኮኖሚ ለማሳለጥ ወጣቶችን በቴክኖሎጂ ለማብቃት ስራ ትኩረት መሰጠቱን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) አስታወቁ። የሰውሰራሽ አስተውሎት ትምህርትን ከአንደኛ ደረጃ ጀምሮ መስጠት የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከኦሮሚያ ክልል ሳይንስና ቴክኖሎጂ ቢሮ ጋር በመተባበር በአምቦ ከተማ ያስገነባው የወጣቶች ኢኖቬሽን ኢንኩቤሽን ማዕከል እና የአምቦ ስታርት አፕ ማዕከል ተመርቋል።   በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፣ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ እና ሌሎች የፌዴራል እና የክልል አመራሮች ተገኝተዋል። በዚሁ ጊዜ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፣ ኢትዮጵያ የጀመረችውን የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ለማስቀጠል ወጣቶችን በቴክኖሎጂ፣ በሳይንስና በፈጠራ ለማብቃት ስራ ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል። ዛሬ በአምቦ ከተማ አገልግሎት የጀመረው ማዕከልም በአገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን የኢኖቬሽን ሥነ-ምህዳር የማጠናከርና የቴክኖሎጂ ክፍተቶችን ለመሙላት ያግዛል ብለዋል።   መሰል የኢኖቬሽን ኢንኩቤሽን ማዕከላት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ተገንብተው የዜጎችን ችግር እየፈቱ መሆኑን ጠቅሰው የአምቦው ማዕከልም ወጣቶችን በቴክኖሎጂ በማብቃት የማኅበረሰቡን ችግር የሚፈቱ የፈጠራ ሥራዎች የሚፈልቁበት ይሆናል ነው ያሉት። የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አወሉ አብዲ በበኩላቸው፤ የአንድን ሀገር ዕድገት ማፋጠን የሚቻለው በቴክኖሎጂ ማገዝ ሲቻል መሆኑን ገልጸዋል።   የክልሉ መንግሥት ግብርናንና ሌሎች ዘርፎችን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የሕዝቡን ኑሮ ለማሻሻልና የሀገሪቱን የዲጂታል ኢኮኖሚ ግብ ለማሳካት ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። የአምቦ ከተማ ከንቲባ አቶ ሃጫሉ ገመቹ፤ ማዕከሉ ወጣቶች የሚዝናኑበት ብቻ ሳይሆን፣ ዕውቀታቸውን ወደ ተግባር በመለወጥ ማኅበረሰባቸውን የሚያገለግሉበት የፈጠራ ማዕከል መሆኑን አብራርተዋል።   በማዕከሉ የቴክኖሎጂ ሥልጠና የወሰዱ ወጣቶች በበኩላቸው፣ ባገኙት ዕውቀት ተጠቅመው የሀገሪቱን ዕድገት ለማፋጠን መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።   በተለይም የድረ-ገጽ ማበልጸግ ሥልጠና በመውሰድ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና ማኅበረሰብን በፈጠራ ለማገዝ መዘጋጀታቸውን ጠቁመዋል።
በከተማዋ በተያዘው በጀት ዓመት ለአንድ መቶ ሺህ ዜጎች የፋይዳ መታወቂያ ለማዳረስ እየተሰራ ነው
Feb 27, 2026 89
ደገሃቡር፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦በሶማሌ ክልል ደገሃቡር ከተማ በተያዘው በጀት ዓመት ለአንድ መቶ ሺህ ዜጎች የፋይዳ መታወቂያ ለማዳረስ እየተሰራ መሆኑን የከተማዋ ከንቲባ አብዲሀኪም መአሊን ገለጹ። የደገሃቡር ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አብዲሀኪም መአሊን ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ዜጎች ወጥ የሆነ ማንነት እንዲኖራቸው በማድረግ የተቀላጠፈና ዘመናዊ አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችል ነው። ፋይዳ መታወቂያን ከተለያዩ አገልግሎቶች ጋር ማስተሳሰር ከተጀመረ ወዲህ የተመዝጋቢዎች ቁጥር እየጨመረ ነው ፋይዳ ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተቀመጠው ሀገራዊ ግብ እንዲሳካና ለዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመት በከተማዋ 100 ሺህ ዜጎችን የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ እስካሁን ከ30 ሺህ በላይ ለሚሆኑት ተደራሽ መደረጉን አመልክተዋል። በከተማ አስተዳደሩ የወጣቶችን የዲጂታል ክህሎት ለማሳደግ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና እየተሰጠ መሆኑንም ተናግረዋል። ስልጠናው በቴክኖሎጂ የዳበረ ወጣት ለመፍጠር የላቀ ሚና እንዳለው ጠቅሰው፣ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ዜጎች የዲጂታል መታወቂያውን በመያዝ ከሚሰጡ ዘመናዊ አገልግሎቶች ተጠቃሚ እንዲሆኑም ጥሪ አቅርበዋል።
መቱ ዩኒቨርሲቲ በሚያካሄደው ማህበረሰብ ተኮር የጥናትና ምርምር ስራዎች የአካባቢውን ነዋሪዎች ተጠቃሚ እያደረገ ነው
Feb 27, 2026 377
መቱ፤ የካቲት 20/2018 (ኢዜአ):- መቱ ዩኒቨርሲቲ በሚያካሄደው ማህበረሰብ ተኮር የጥናትና ምርምር ስራዎች የአካባቢውን ነዋሪዎች ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን አስታወቀ። በዩኒቨርሲቲው የጥናትና ምርምር ዳይሬክቶሬት የግብርና ምርምር ዘርፍ አስተባባሪና መምህር ነዚፍ ሀምዛ ለኢዜአ እንዳሉት ዩኒቨርሰቲው ከመማር ማስተማር ጎን ለጎን በቴክኖሎጂ በመታገዝ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት በማካሄድ የማህበረሰቡን ችግር ለመፍታት እየሰራ ይገኛል። ዩኒቨርሲቲው የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ በግብርና መስኮች ጥናትና ምርምር እያካሄደ ሲሆን ውጤቶችንም ወደ ተጨባጭ ስራ ለመቀየር ዘጠኝ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ለተግባራዊነቱ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።   ከፕሮጀክቶቹ መካከል የሰብል እና የሆርቲካልቸር ምርጥ ዘር ዝግጅትና ብዜት፣ የእንስሳት ዝርያ ማሻሻያ እንዲሁም ቨርሚ ኮምፖስት ቴክኖሎጂን ማስረጽ እንደሚገኙበት አስረድተዋል። በተለይ በሰብል ልማት እና በሆርቲካልቸር ከአከባቢው የአየር ንብረት ጋር ተስማሚ እና ምርታማነታቸው የተረጋገጠ ዝርያዎችን ለማባዛትና ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። የፕሮጀክቶቹ ዋና ዓላማ የመማር ማስተማር ስራውን በተግባር የተደገፈ ከማድረግ ባለፈ የአካባቢው ማህበረሰብን ተጠቃሚ ማድረግ መሆኑን ጠቅሰዋል። እንዲሁም መንግስት ዩኒቨርሲቲዎች በውስጥ አቅም ራሳቸውን እንዲችሉ ያስቀመጠውን አቅጣጫ ለማሳካት ጭምር መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ዩኒቨርሲቲው የተጣለበትን ሀገራዊ ተልዕኮ በብቃት ለመወጣት እና የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትናን እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ እንደሚያስችል አስረድተዋል።   በዩኒቨሲቲው የዕጽዋት ሳይንስ መምህርና ተመራማሪ መምህር ምስጋኑ ዋቅጅራ በበኩላቸው በምርምር የተገኘ ምርጥ የበቆሎ ዝርያን ለአርሶ አደሮች ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ለዚህም በ2017/2018 መኸር ከኢትዮጵያ የግብርና ግብአቶች ኮርፖሬሽን የነቀምቴ ቅርንጫፍ ጋር በመተባበር በ30 ሔሄታር መሬት ላይ የማባዛት ስራ መሰራቱን ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅት የምርት መሰብሰብ ስራው ተጠናቆ ለዘር የሚሆን 600 ኩንታል በቆሎ በማዘጋጀት ለተጠቃሚዎች ተደራሽ እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   በዩኒቨርሲቲው የሆርቲካልቸር ዘርፍ መምህርና ተመራማሪ ሳሙኤል ታዬ ዩኒቨርሲቲው በግብርናው ዘርፍ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የችግኝ ጣቢያዎችን በማዘጋጀት ለመማር ማስተማር፣ ለጥናትና ምርምር እንዲሁም ለማህበረሰብ አገልግሎትና ትስስር ስራዎቹ እየተጠቀመበት መሆኑን አንስተዋል። ይህም ዩኒቨርሲቲው የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማትና የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ ሀገራዊ ግቦች ለማሳካት የበኩሉን ድርሻ ለማበርከት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ወጣት ተመስገን ሂካ፣ መልካሜ ተሾመ እና አቶ ብርሃኑ ማሞ በፕሮጀክቱ ችግኝ ጣቢያዎች የስራ እድል የተፈጠረላቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ሲሆኑ በስራው በሚያገኙት ገቢ ሕይወታቸውን እየመሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።   ያገኙትን ልምድ በመታገዝ የራሳቸውን ችግኝ ጣቢያ በማቋቋም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ማቀዳቸውን ተናግረዋል።    
ኢንስቲትዩቱ የዓሣ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የዝርያ ማሻሻልና ተጓዳኝ ስራዎች እያከናወነ ነው
Feb 27, 2026 69
አዳማ፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦ የኦሮሚያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የዓሣ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የዝርያ ማሻሻልና ሌሎች ተጓዳኝ ስራዎች እያከናወነ መሆኑን አስታወቀ። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ተሾመ ቦጋለ ለኢዜአ እንደገለጹት የዓሣ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት ለማሳካት በዓሣ ዝርያ ማሻሻያ ላይ ኢንስቲትዩቱ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል። በተለይ እየተተገበረ ያለውን የዓሣ ልማት ኢንሼቲቭ ለማሳካት ምርቱን የሚጨምሩ ዝርያዎችን በስፋት ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በክልሉ የውሃ አካላት በሙሉ የዓሣ ምርት መያዝ አለባቸው የሚል ግብ ተቀምጦ በዝርያ ማሻሻያ ላይ የምርምር ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አመልክተዋል። ኢንስቲትዩቱ በምርምር ማዕከላቱ የዓሣ ጫጩት የማባዛት ስራ እየሰራ መሆኑንና የተባዙ የዓሣ ጫጩቶችን ለአርሶ አደሩ በነፃ እየተሰራጨ መሆኑንም አክለዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያው ግማሽ ዓመት ከ1 ሚሊየን በላይ የዓሣ ጫጩቶች መሰራጨታቸውን ጠቅሰዋል። በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ 5 ሚሊየን የዓሣ ጫጩቶች ለማሰራጨት የተያዘውን እቅድ ለማሳካት ጥረት እየተደረገ እንደሆነ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የባቱ የዓሣ ምርምር ማዕከልን ጨምሮ በኢንስቲትዩቱ ስር በሚገኙ የምርምር ማዕከላት ብዛት ያላቸው የዓሣ ጫጩት ዝርያዎች መባዛታቸውን ጠቁመው የዓሣ ጫጩት ብዜት ስራው በቤተ ሙከራና በኩሬ እየተከናወነ መሆኑን አመልክተዋል። ከዝርያ ማሻሻያ ስራዎች በተጓዳኝ ከዓሣ እርባታ ጋር በተያያዘ የእውቀትና የአሰራር ክህሎት ስልጠናና አቅም ግንባታም እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይ በሀገር ደረጃ የተያዘውን በምግብ ራስን የመቻልና የስነ ምግብ ስርዓትን ለማስረፅ የዓሣ ሀብት ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የጎላ ሚና አለው ብለዋል። በዚህም የህፃናት የአእምሮ እድገት እንዲጎለብት፣ የመቀንጨርና መቀጨጭ ችግሮችን ለመቅረፍ ዓሣ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።
በዋትስአፕ መተግበሪያ ላይ እየተፈጸሙ ያሉ የተቀናጁ የጠለፋ ጥቃቶችን በተመለከተ ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የተላለፈ አስቸኳይ የጥንቃቄ መልዕክት
Feb 27, 2026 130
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ከዚህ ቀደም በተለያዩ ጊዜያት የዜጎችንና የተቋማትን የሳይበር ደህንነት ለማስጠበቅ ተደጋጋሚ የጥንቃቄ መልዕክቶችን ለማህበረሰቡ ሲያስተላልፍ መቆየቱ ይታወሳል። በተለይ ከዋትስአፕና ከቴሌግራም አካዉንቶች ጠለፋ መስፋፋትን ተከትሎ በቅርቡም የጥንቃቄ መልዕክት ማስተላለፉ ይታወቃል። ሆኖም በአሁኑ ወቅት በሀገራችን ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በተለይም ሰባተኛውን ጠቅላላ የምርጫ ሂደትን ተገን በማድረግ፣ አጥፊዎች ስልታቸውን ይበልጥ በማወሳሰብ የዋትስአፕ ተጠቃሚዎችን ኢላማ ያደረገ ሰፊ የሳይበር ጥቃት እየፈጸሙ እንደሚገኝ አስተዳደሩ በሚደርሱት መረጃዎችና የሳይበር ደህንነት ትንተናዎች ማረጋገጥ ችሏል። ይህ ጥቃት በተለይ ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎችን፣ በውጭ ሀገር የሚኖሩ ተማሪዎችን፣ በርቀት ሆነዉ በዲጂታል አማራጮች የሚማሩ ግለሰቦችን እና ተፅዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦችን ኢላማ ያደረገ በመሆኑ፣ መላው የዋትስአፕ ተጠቃሚ ማህበረሰብ ሊያውቃቸው የሚገቡ የጥቃት ስልቶችና የመከላከያ መንገዶች እንደሚከተለው ቀርበዋል፦ የመረጃ መንታፊዎች የሚጠቀሙባቸዉ ዋና ዋና የጠለፋ ስልቶች 1. የምርጫ ሂደትን እና የፖለቲካ ኩነቶችን ለሴራ መጠቀም፦ አጥፊዎቹ የሀገራዊ የምርጫ ወቅት መሆኑን እንደ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም የዜጎችን የፖለቲካ ፍላጎትና ስሜት ለጥቃት መቹ አጋጣሚ አድርገዉ እየተጠቀሙ ይገኛል፦ የምርጫ ደጋፊ በመምሰል፦ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ደጋፊ በመምሰልና የፓርቲዎችን አርማ (Logo) በመጠቀም "ለፓርቲያችን ድጋፍዎን እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን ይግለጹ" ወይም "የምርጫ ቅስቀሳ ቡድናችንን ይቀላቀሉ" የሚሉ አሳሳች መልዕክቶችን ይልካሉ። የምርጫ መረጃ አቅራቢ በመምሰል፦ "የምርጫ ጣቢያዎትን ለማወቅ"፣ "የዕጩዎችን ዝርዝር ለማየት" ወይም "የምርጫ ውጤቶችን በቅድሚያ ለማግኘት" የሚሉ አሳሳች ማስፈንጠሪያዎችን (Links) በመጠቀም የተጠቃሚዎችን የዋትስአፕ አካውንት በቁጥጥራቸው ስር ያውላሉ። 2. ተከታታይ ጠለፋ እና የማንነት ስርቆት: ይህ ስልት እጅግ አደገኛ የሆነው ጥቃቱ የሚመጣው ከሚታወቅና ከቅርብ ሰው በመሆኑ ነው። የአንድ ግለሰብ አካውንት አንዴ ከተጠለፈ በኋላ አጥፊዎቹ የሚከተሉትን ድርጊቶች ይፈጽማሉ፦ የገንዘብ ማጭበርበር፦ የተጠለፈውን ሰው ማንነት በመጠቀም በስልክ አድራሻ ዝርዝሩ ውስጥ ላሉ ወዳጆች "ድንገተኛ የጤና ችግር አጋጥሞኝ ነው" ወይም "ከምርጫ ስራ ጋር በተያያዘ ገንዘብ በአስቸኳይ አስፈልጎኝ ነው" በማለት የባንክ አካውንት በመላክ ከፍተኛ የገንዘብ ማጭበርበር ይፈጽማሉ። ተጨማሪ ጠለፋ፦ ለሌሎች የሥራ ባልደረቦችና ኃላፊዎች አሳሳች ሊንኮችን በመላክ የጥቃቱን ሰለባ ያስፋፋሉ። በዚህም ወሳኝ የሆኑ የመንግስት እና የተቋማዊ መረጃዎችን የመስረቅና የማጥፋት ስጋት ይፈጥራሉ። 3. ተማሪዎችን እና የከፍተኛ ትምህርት ተከታታዮችን ኢላማ ማድረግ፦ በውጭ ሀገር የሚማሩ ወይም በኢንተርኔት ትምህርታቸውን የሚከታተሉ ዜጎችን ኢላማ በማድረግ፤ ከሚማሩበት ዩኒቨርሲቲ የተላከ በማስመስል (ለቪዛ እድሳት፣ ለትምህርት ክፍያ ቅናሽ ወይም ለፈተና መረጃ በሚል ሰበብ) ሊንኮችን ይልካሉ። ተማሪዎቹ መረጃቸውን ሲያስገቡ የግል መረጃቸውና የዋትስአፕ አካውንታቸው ወዲያውኑ ይረበሻል። 4. የባለ 6-አሃዝ ኮድ ማጭበርበር: አጥፊዎች የእርስዎን ስልክ ቁጥር በመጠቀም በሌላ ስልክ ዋትስአፕ ለመክፈት ይሞክሩና ወደ እርስዎ ስልክ በቴክስት (SMS) የሚመጣውን ባለ 6-አሃዝ ኮድ፤ "በስህተት ወደ አንተ የተላከ ኮድ ስለሆነ እባክህ መልሰህ ላክልኝ" በማለት ይጠይቃሉ። ይህንን ኮድ አሳልፈው ከሰጡ አካውንትዎ ወዲያውኑ ይጠለፋል። ራስን እና ተቋምን ለመጠበቅ መወሰድ ያለባቸው እርምጃዎች 1. ባለሁለት-ደረጃ ማረጋገጫን ያብሩ፦ ይህ አካውንትዎን ከጠለፋ ለመጠበቅ ቁልፍ መከላከያ ነው። እንዴት ይበራል? WhatsApp Settings > Account > Two-step verification > Turn On በመግባት የራስዎን ሚስጥራዊ ባለ 6-አሃዝ ቁጥር (PIN) እና የኢሜይል አድራሻ ያስገቡ። 2. የማረጋገጫ ኮድን በምንም ምክንያት አያጋሩ፦ ወደ ስልክዎ በሜሴጅ የሚላክን የዋትስአፕ ማረጋገጫ ኮድ (Verification Code) ለምንም አይነት አካል (ለጓደኛም ሆነ ለቤተሰብ) አሳልፈው አይስጡ። 3. አጠራጣሪ ሊንኮችን (Links) አይጫኑ፦ በተለይ ከምርጫና ወቅታዊ ጉዳዮች ጋር ተያይዞ ከማይታወቅም ሆነ ከሚታወቅ ሰው የሚላኩልዎትን አጠራጣሪ ሊንኮች ከመጫንዎ በፊት ትክክለኛነቱን በሌላ የመገናኛ ዘዴ ያረጋግጡ። 4. የገንዘብ ጥያቄን በመደበኛ ስልክ ያረጋግጡ፦ ማንኛውም ሰው በዋትስአፕ በኩል የገንዘብ እርዳታ ሲጠይቅዎት፣ አካውንቱ ተጠልፎ ሊሆን ስለሚችል ገንዘብ ከመላክዎ በፊት በመደበኛ ስልክ በመደወል ድምፁን ሰምተው ትክክለኛነቱን ያረጋግጡ። 5. የመረጃ ጥንቃቄ ያድርጉ፦ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች ወሳኝ የሆኑ ሀገራዊ እና ተቋማዊ መረጃዎችን በዋትስአፕ ከመለዋወጥ መቆጠብ አለባቸው። ለሥራ ጉዳይ ደህንነታቸው የተረጋገጡ (Secure) የውስጥ መገናኛ ዘዴዎችን መጠቀም ይመከራል። አካውንትዎ ከተጠለፈ ምን ማድረግ አለብዎት? ወዲያውኑ ድጋሚ ለመመዝገብ ይሞክሩ፦ የዋትስአፕ መተግበሪያዎን አጥፍተው (Uninstall) እንደገና በመጫን ስልክ ቁጥርዎን ያስገቡ። በSMS የሚላክልዎትን ኮድ ሲያስገቡ አጥፊው ከእርስዎ አካውንት በራስ-ሰር እንዲወጣ (Log out) ይደረጋል። ለወዳጅ ዘመዶችዎ መልዕክት ያስተላልፉ፦ አካውንትዎ ተጠልፎ እንደነበር በመደበኛ ስልክ ወይም በሌሎች አማራጮች በማሳወቅ፣ ከእርስዎ ስም ለሚመጣ ማንኛውም የገንዘብም ሆነ የሊንክ ጥያቄ ምላሽ እንዳይሰጡ ያስጠነቅቁ። ሪፖርት ያድርጉ፦ ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊ ከሆኑ ወይም ጥቃቱ ተቋማዊ ጉዳት የሚያስከትል ከሆነ ጉዳዩን ወዲያውኑ ለኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ሪፖርት ያድርጉ። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የሀገሪቱን የሳይበር ምህዳር ደህንነት ለማስጠበቅ የሚሰራቸውን ስራዎች አጠናክሮ የሚቀጥል ሲሆን፣ ህብረተሰቡም አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ለሳይበር ሌቦች በር እንዳይከፍት ያሳስባል። ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር የካቲት 20/2018 ዓ.ም አዲስ አበባ
የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን አገልግሎቶቹን ሙሉ በሙሉ ዲጂታላይዝ አድርጓል
Feb 26, 2026 155
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- የሀገሪቱን የገቢና ወጪ ንግድ ሥርዓት ለማቀላጠፍና ቁጥጥሩን ለማዘመን አገልግሎቶቹን ሙሉ በሙሉ በዲጂታል ቴክኖሎጂ ማድረጉን የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን አስታወቀ። ኢትዮጵያ በዲጂታል 2025 ስትራቴጂ በርካታ ውጤታማ የዲጂታላይዜሽን ተግባራትን አከናውናለች። ይህንንም አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያስችለው ዲጂታል 2030 ስትራቴጂ ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል። ኢትዮጵያ ዲጂታል ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነች ነው በዲጂታል 2025 በርካታ ተቋማት አገልግሎታቸውን ያዘመኑ ሲሆን በአሁኑ ወቅት በዲጂታል የተደገፈ የተቀላጠፈ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ። የጉምሩክ ኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር አዘዘው ጫኔ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኮሚሽኑ ዲጂታል 2025 ተከትሎ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ አተኩሮ በርካታ ውጤታማ ተግባራት በማከናወን የሚሰጡ አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝ ማድረግ ተችሏል፡፡፡ በአሁኑ ወቅት ነጋዴዎች በማንኛውም ቦታ ሆነው የጉምሩክ ሥርዓትን መፈጸም የሚችሉበት የተቀናጀ የዲጂታል ሥርዓት መዘርጋት መቻሉን አስታውቀዋል። ከ70 በላይ ተቋማትን በአንድ ላይ የሚያገናኘው የኤሌክትሮኒክ ሲንግል ዊንዶው ፕላትፎርም ተግባራዊ መድረጉን አንስተው፤ ይህም የንግድ ስራን ለማቀላጠፍ ትልቅ እመርታ መሆኑን ተናግረዋል። የኮሚሽኑን የክትትል አቅም ለማሳደግ ስማርት ቦርደር ማኔጅመንት ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል ሲሉም አንስተዋል፡፡ የኤሌክትሮኒክ ካርጎ ትራኪንግ ሲስተምን በመጠቀም ጭነቶች ካለባቸው መስመር እንዳይወጡ ጥብቅ ቁጥጥር እየተደረገ እንደሚገኝም ምክትል ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል፡፡ በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዙ ካሜራዎች በተለያዩ ስልታዊ ቦታዎች ላይ ተተክለው ውጤታማ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ምክትል ኮሚሽነሩ ኮሚሽኑ ከንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር፣ ከባንኮችና ከሌሎች ፈቃጅና ተቆጣጣሪ ተቋማት ጋር በቴክኖሎጂ ትስስር መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡ በሀገር ውስጥ የታክስ ሥርዓትም የኢ-ፋይሊንግ እና የኢ-ፔይመንት አገልግሎቶች ሙሉ በሙሉ ስራ ላይ ውለዋል ብለዋል። እንደ ምክትል ኮሚሽነሩ ገለጻ በአሁኑ ወቅት በጂቡቲ የሚገኙ ሁለት ቅርንጫፎችን ጨምሮ በመላ ሀገሪቱ ያሉ 15 ቅርንጫፎች በሙሉ በቴክኖሎጂ የተደገፈ የ24 ሰዓት አገልግሎት በቴክኖሎጂ በመስጠት ላይ ይገኛሉ። ይህ መጠነ ሰፊ የዲጂታላይዜሽን ስራ የገቢና ወጪ ንግዱን ከማሳለጡ ባለፈ፣ የህግ ማስከበር ስራውን በቴክኖሎጂ የታገዘና ግልጽ አሰራረን ተግባራዊ በማድረግ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚደግፍ አስታውቀዋል።
እያደገ የመጣው የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂ በዜጎች ኑሮ ላይ ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል
Feb 26, 2026 77
ደብረ ማርቆስ ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን እያደገ የመጣው የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂ ተደራሽነት የዜጎች ኑሮ ላይ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱ ተገለጸ። የገጠር መሬትን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር አርሶአደሩ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሰራ ነው ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የምስራቅ ጎጃም ዞን አርሶ-አደሮች፤ አማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀማቸው የደን ጭፍጨፋን መቀነስ፣ ጤናቸውን መጠበቅና ምርታማነታቸውን ማሳደግ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። የጎዛምን ወረዳ ደሳ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ጌታቸው አንሙት፣ የባዮጋዝ ቴክኖሎጂን በመገንባት ለምግብ ማብሰያና ለመብራት አገልግሎት መጠቀም መጀመራቸውን ተናግረዋል። ይህም ቀደም ሲል ለማገዶና ለናፍጣ ሳወጣ የነበረውን ወጪ ቆጥቦልኛል ብለዋል። አማራጭ የኢነርጂ ቴክኖሎጂው የእርሳቸውንና ቤተሰባቸውን ጤና እንዲጠብቁ ከማድረግ ባለፈ ማገዶ ፍለጋ ጫካ በመሄድ ይደረስባቸው የነበረውን እንግልት መቀነሱን ገልጸዋል። አርሶ አደር ጌታሁነኝ ብርሃን በበኩላቸው፣ ከባዮጋዝ የሚገኘውን ተረፈ ምርት እንደ ማዳበሪያ በመጠቀማቸው የአትክልትና ሰብል ምርታማነታቸው መጨመሩን ገልጸዋል። ቴክኖሎጂውን ለተለያዩ አገለግሎቶች እያዋሉት መሆኑንና በዚህም በኑሯቸው ላይ ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን አንስተዋል። የእነደድ ወረዳ ነዋሪ ዘውዲቱ ጥላሁን፣ ዘመናዊና ሀይል ቆጣቢ ምድጃዎችን መጠቀም መጀመራቸው ከዚህ ቀደም በእሳት ነበልባልና በጭስ ምክንያት ይደርስባቸው ከነበረው የጤና መታወክ እንደታደጋቸው ገልጸዋል። የምስራቅ ጎጃም ዞን ውሃና ኢነርጅ መምሪያ ሃላፊ ፍሬው ካሴ እንደገለጹት፤ በዞኑ አማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂ ተደራሽነትን በማስፋት የአርሶአደሩን ኑሮ ለማሻሻል ጥረት እየተደረገ ነው። በ2018 በጀት ዓመት ከ44ሺህ በላይ የተለያዩ የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ ለማድረግ ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን አስታውሰው፣አሁን ላይ ከ34 ሺ በላይ ቴክኖሎጂዎች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጋቸውን ተናግረዋል። ከአማራጭ የሃይል ቴክኖሎጂዎች ውስጥ 21 ሺህ 243ቱ ማገዶ ቆጣቢ ምድጃዎች፣ 13 ሺህ 451ዱ በጸሃይ ሃይል የሚሰሩና 261ዱ የባዮጋዝ ቴክኖሎጂ ግንባታ ይገኙበታል ብለዋል። በቴክኖሎጂዎቹ ከ140 ሺ በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ መሆናቸውንና በዚህም የደን ጭፍጨፋን መከላከልና የሕብረተሰቡን ጤና መጠበቅ እንደተቻለ አመልክተዋል። በዞኑ እስካሁን አንድ ሚሊዮን የሚጠጉ የተለያዩ የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂዎች ለህብረተሰቡ ተደራሽ መሆናቸውን የመምሪያው መረጃ ያመለክታል።
የሰውሰራሽ አስተውሎት ትምህርትን ከአንደኛ ደረጃ ጀምሮ መስጠት የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው
Feb 26, 2026 110
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ የሰውሰራሽ አስተውሎትና የዲጂታል ክህሎት ማሳደጊያ ትምህርትን ከአንደኛ ደረጃ ጀምሮ መስጠት የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የትምህርት ሚኒስቴር ገለፀ። በትምህርት ሚኒስቴር የኢ-ለርኒንግና የ5 ሚሊየን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ አስተባባሪ ሙሉነህ አጥናፉ ለኢዜአ እንዳሉት፥ በሀገሪቱ እየተተገበሩ ያሉ የሪፎርም ስራዎችን ለማሳለጥና ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትግበራ ውጤታማነት የሰው ኃይል ልማት ወሳኝ ነው። የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ የወጣቱን የዲጂታል፣ የሳይንስና ቴክኖሎጂ አቅም ማጎልበት ወሳኝ ነው ለዚህም የዲጂታል ክህሎትና እውቀትን ማበልፀግ እንደሚያስፈልግ አንስተው ሚኒስቴሩ ሀገራዊ የሪፎርም አጀንዳዎችንና ተልዕኮውን መሰረት ያደረገ ጉዞ መጀመሩን ተናግረዋል። የመምህራንና ተማሪዎችን እንዲሁም የህብረተሰቡን የዲጂታል እውቀትና ክህሎት ማሳደጊያ መርኃ ግብሮችን ለመተግበር እየተሰራ መሆኑንም ገልፀዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች አንዱ የሆነው የሰውሰራሽ አስተውሎት መሆኑን አንስተው ዘርፉ ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ የሚያበረክተውን ጠቀሜታ ማረጋገጥ የሚያስችል ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። የሰውሰራሽ አስተውሎትና የዲጂታል ግንዛቤን የሚያሳድግ ትምህርት ከአንደኛ እስከ 12ኛ ክፍል ድረስ በስርዓተ ትምህርት ውስጥ በማካተት ለመስጠት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚገኙ መምህራንና ተማሪዎችን የዲጂታል ክህሎትና እውቀት ማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝም ተናግረዋል። ለዚህም የ5 ሚሊየን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ስልጠና እንዲወስዱ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ጨምረው አስረድተዋል። ትምህርት ሚኒስቴር ከዲጂታሉ ዓለም ጋር ብቁና ተወዳዳሪ ሆነው የሚራመዱ ታዳጊዎችንና ወጣቶችን ለማፍራት የዲጂታል እውቀትና ክህሎት መሠረቶች ላይ ትኩረት መስጠቱንም ገልጸዋል፡፡
ፋይዳ መታወቂያን ከተለያዩ አገልግሎቶች ጋር ማስተሳሰር ከተጀመረ ወዲህ የተመዝጋቢዎች ቁጥር እየጨመረ ነው
Feb 26, 2026 140
አሶሳ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያን ከተለያዩ አገልግሎቶች ጋር ማስተሳሰር ከተጀመረ ወዲህ የተመዝጋቢዎች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የምዝገባ አስተባባሪ ደጀኔ ገብሬ አስታወቁ። በ2014 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የተጀመረው የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከተለያዩ አገልግሎቶች ጋር በማስተሳሰር የዲጂታል መሠረተ ልማትን ለማሳለጥ እየተሰራ ይገኛል። በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከ160 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ደምበኞች የተቀላጠፈ አገልግሎት ተሰጥቷል የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የምዝገባ አስተባባሪ ደጀኔ ገብሬ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ አካታች እንዲሆን ከተለያዩ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ጋር በቅንጅት እንዲሰራ ተደርጓል። በዚህም የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ተመዝጋቢዎች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን ገልፀው፤ የምዝገባ ፕሮግራሙ ከተጀመረ ወዲህ 36 ሚሊዮን ዜጎች ተመዝግበው የመታወቂያው ባለቤት መሆናቸውን ገልጸዋል። ፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ የአገልግሎት አሰጣጥን የሚያቀላጥፍ እና ለሀገር ኢኮኖሚ ግንባታ ዓይነተኛ ሚና እያበረከተ እንደሆነ ጠቁመው፤ በተለይም የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን ከግብ ለማድረስ ጉልህ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል። ለአብነትም ፋይዳን ከአርሶ አደሩ የመሬት ባለቤትነት ጋር ማስተሳሰር በርካታ ዜጎች እንዲመዘገቡ ከማድረግ ባለፈ አርሶ አደሩ ይዞታውን አስይዞ የፋይናንስ አቅርቦት እንዲያገኝ እና ማሳውን በአግባቡ ለማስተዳደር እንደሚያግዘው አንስተዋል። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እስካሁን ከ250 ሺህ በላይ ዜጎች የተመዘገቡ ሲሆን አፈጻጸሙን ለማሻሻል የህብረተሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ እንደሚያስፈልግም አስተባባሪው አስታውቀዋል። በክልሉ የመቶ ፐርሰንት ግብ አፈጻጸም ዝቅተኛ በመሆኑ ከተለያዩ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ጋር በማስተሳሰር ዕቅዱን ማሳካት እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መሬትና ህብረት ስራ ማደራጃ ቢሮ ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር "ብሔራዊ መታወቂያ ለገጠር መሬት ባለይዞታዎች" በሚል መሪ ሃሳብ የምክክር መድረክ መካሄዱ ይታወሳል።
የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የደንበኞችን መረጃ የሚያዘምን ፕሮጀክት ማስጀመሩን አስታወቀ
Feb 25, 2026 98
አዲስ አበባ ፤የካቲት 18 /2018 (ኢዜአ)፡- የአዲስ አበባ ከተማ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የደንበኞች መረጃ የሚያዘምን የፕሮጀክት ሙከራ ትግበራ ማስጀመሩን አስታወቀ። ባለስልጣኑ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር የደንበኞች አገልግሎቶች በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ሥርዓት የተደገፉ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን በማስመልከት ለመገናኛ ብዙኅን መግለጫ ሰጥቷል።   መግለጫውንም በባለሥልጣኑ የአገልግሎት ዘርፍ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ሞገስ አርጋው እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተወካይና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ፕሮፌሰር ገረመው ሳህሌ በጋራ ሰጥተዋል። አቶ ሞገስ አርጋው በዚህ ወቅት፤ የደንበኞችን የውሃ አቅርቦት አገልግሎቶች በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ማስተሳሰር የሚያስችል የአሰራር ሥርዓት ተግባራዊ እየተደረገ ነው ብለዋል። የደንበኞች መረጃ ማዘመን ፕሮጀክት ትግበራም የቢል፣ ማህደርና የመሬት መረጃዎችን በማጣጣም ዘመናዊ ቀልጣፋ፣ ወጪ ቆጣቢና የውሃ ብክነትን የሚቀንስ አገልግሎቶችን ለመስጠት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። የፕሮጀክቱ ዋና ዓላማም የተሟላ፤ ትክክለኛና ወቅታዊ መረጃ በማደራጀት አሠራርን ዲጂታላይዝ በማድረግ የተቀላጠፈ የመስመር ላይ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል።   የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ተወካይና የፕሮጀክቱ አስተባባሪ ፕሮፌሰር ገረመው ሳህሌ በበኩላቸው፤ ፕሮጀክቱ የውሃ አገልግሎቶችን የሚያሳልጥ የስማርት ሲቲ ግንባታ አካል መሆኑን ገልጸዋል። የፕሮጀክቱም የውሃና ሳኒቴሽን ሥርዓትን በማዘመን የባለስልጣኑን ተለምዷዊ አገልግሎት አሰጣጥ መቀየር የሚስችል ምኅዳር የሚፈጥርና ዘላቂነት የሚያረጋግጥ መሆኑን ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የደንበኞች መረጃ የሚያዘምነው ፕሮጀክትም በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4 እና 5 እንዲሁም በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 በይፋ የተጀመረ ሲሆን በቀጣይም ተደራሽነቱን ለማስፋት እንደሚሰራ ተጠቁሟል።  
በፌዴራል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የዜጎች እርካታ 98 ነጥብ 7 በመቶ ደርሷል
Feb 25, 2026 151
አዲስ አበባ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦የፌዴራል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ባለፉት 10 ወራት የዜጎችን የአገልግሎት እርካታ 98 ነጥብ 7 ማድረሱን የአገልግሎቱ ዳይሬክተር ጄኔራል አንተነህ ማሞ ገለጹ። አገልግሎቱ በተበታተነ መልኩ የሚሰጡ አሰራሮችን በአንድ ጣሪያ ስር በማምጣት እስካሁን ከ160 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቀልጣፋና ዘመናዊ አገልግሎት መስጠቱንም ጠቅሰዋል። በማዕከሉ የተለያዩ አገልግሎቶችን ያገኙ አስተያየት ሰጪዎች በበኩላቸው ባጠረ ጊዜ ቀልጣፋ አገልግሎት በማግኘት ጉዳያቸውን በአግባቡ መፈጸማቸውን ተናግረዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተቋቋመው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በተበታተነ መልኩ የሚሰጡ አገልገሎቶችን በአንድ ቦታ ማግኘት የሚያስችል አሰራር ነው። የፌዴራል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራል አቶ አንተነህ ማሞ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ማዕከሉ ተቋማት በዲጂታል ቴክኖሎጂ ታግዘው በአንድ ቦታ አገልግሎት እንዲሰጡ የሚያስችል አሰራር ነው። አገልግሎቱ ከተጀመረ በ10 ወራት ውስጥ በርካታ ማዕከላትን በማቋቋም ለዜጎች ግልፅ፣ ቀልጣፋና እርካታን ያሳደገ አገልግሎት መስጠት መቻሉን ተናግረዋል። ይህም ዜጎች በአንድ ቦታ፣ ባጠረ ጊዜና በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በተደገፈ አሰራር አገልግሎት እንዲያገኙ በማስቻል ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ከተጀመረ ወዲህም በአገልግሎቱ የዜጎች እርካታ 98 ነጥብ 7 በመቶ መድረሱን ጠቁመዋል። ወደ መሶብ ያልገቡ ተቋማት የአሠራሩ አካል እንዲሆኑና ለአገልግሎት ጥራት መሻሻል የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። ለዚህም አዲስ አበባን ጨምሮ በሁሉም ክልሎችና ከተሞች አገልግሎቱን በጥራት ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቶታል ነው ያሉት። ዳይሬከተሩ አክለውም፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሰጡት አቅጣጫ መሰረት የ24 ሰዓት አገልግሎት ለመስጠት በቁርጠኝነት እየተሠራ ስለመሆኑም ገልጸዋል። ንግድ ፍቃድ ለማውጣት ወደ ማዕከሉ የመጡት ተገልጋይ አደመ አየለ በሰጡት አስተያየት ቀደም ሲል የነበረው የተጓተተ ንግድ ፍቃድ የማውጣት ሂደት በመቀረፉ መደሰታቸውን ተናግረዋል።   በተቋማት መካከል የተቀናጀና የተቀላጠፈ አሠራር መዘርጋቱ እንግልትንና ምልልስን አስቀርቷል ነው ያሉት። ለኢሚግሬሽንና የዜግነት አገልግሎት የመጡት ቤተልሔም እንግዳ፥ በማዕከሉ በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘታቸውን ጠቁመዋል።   መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ለህብረተሰቡ እርካታን የሚፈጥር ውጤታማ አሠራር በመሆኑ ዜጎች የዚህ ዘመናዊ አሰራር ተጠቃሚ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል።
የገጠር መሬትን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር አርሶአደሩ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሰራ ነው
Feb 25, 2026 314
አሶሳ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦ የገጠር መሬትን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር አርሶአደሩ የኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሰራ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መሬትና ህብረት ስራ ማደራጃ ቢሮ ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር "ብሔራዊ መታወቂያ ለገጠር መሬት ባለይዞታዎች" በሚል መሪ ሃሳብ የምክክር መድረክ አካሂዷል።   በግብርና ሚኒስቴር የገጠር መሬት አስተዳደር እና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈጻሚ አቶ ትዕግስቱ ገብረመስቀል እንደገለፁት፤ የገጠር መሬትን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር የአርሶ አደሩን ዘላቂ የመሬት ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እና ብልሹ አሰራርን ማስቀረት ይቻላል። አርሶ አደሩ ማሳውን አስይዞ የብድር አገልግሎት እንዲያገኝ በማድረግ ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግ እንዲችልም የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ካሉት ከ50 ሚሊዮን በላይ የአርሶ አደር ማሳዎች መካከል 32 ሚሊዮን ለሚሆኑት የባለቤትነት ይዞታ መሰራቱን ለአብነት አንስተዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጌታሁን አብዲሳ በበኩላቸው፤ የገጠር መሬትን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር የማስተሳሰሩ ሂደት አርሶ አደሩን በተሻለ መልኩ ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው ብለዋል።   ይህም በሀገር አቀፍ ደረጃ ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመተግበር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር እንደሆነም አስረድተዋል። ትግበራው የመሬት አስተዳደርን በዲጂታል ቴክኖሎጂ እንዲካሔድ በማድረግ አለመግባባቶችን ለመፍታት የሚያስችል ሲሆን መሬትን ለተፈለገው አገልግሎት ለመጠቀም ጉልህ ሚና እንደሚኖረው ጠቅሰዋል። የክልሉ መሬትና ህብረት ሥራ ማደራጃ ቢሮ ኃላፊ አቶ ካሚል ሀሚድ በበኩላቸው፤ ‎በክልሉ ለ277 ሺህ 274 ማሳዎች ቋሚ የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር መሠጠቱን ነው የተናገሩት።   ‎አርሶ አደሩ የመሬት ባለቤትነት መብቱን በመጠቀም ማሳውን በማልማት፣ በማከራየት እንዲሁም ከባንክ ጋር በማስተሳሰር የብድር አቅርቦት ማግኘት እንደሚችል ጠቁመዋል። በመድረኩ ላይ የፌዴራል፣ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እና የዘርፉ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ ዲጂታል ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነች ነው
Feb 24, 2026 154
አዲስ አበባ፤ የካቲት 17/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂን በመገንባትና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ላይ እያሳየችው ያለው እመርታ ዲጂታል ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን የዓለም አቀፍ ደህንነት ተመራማሪ እና የባሊሲሊ የዓለም አቀፍ ጉዳዮች ትምህርት ቤት ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አን ፊትዝ-ጄራልድ ገለጹ። ፕሮፌሰር አን ፊትዝ-ጄራልድ ለኢዜአ እንደገለፁት፣ ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት እና በዳታ ላይ የተመሰረቱ መፍትሄዎችን ማምጣት የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነች ነው። ኢትዮጵያ በዲጂታል ትስስርና በመሠረተ ልማት አስደናቂ ሥራ እያከናወነች ነው ይህም እንደ ግብርና፣ ደን ልማት እና ማዕድን ባሉ ዘርፎች ውስጥ ማካተቷ የወደፊት ኢኮኖሚዋን ለማጠናከር ቁልፍ መሳሪያ ነው ብለዋል።   ለዚህ ስኬት ሰው ሰራሽ አስተውሎት(AI) እና የዳታ አያያዝ፣ የሳይበር ደህንነት ጥበቃ፣ የፈጠራ ባለቤትነትና የደረጃዎች ቁጥጥር እንዲሁም የኳንተም ቴክኖሎጂ የኮምፒውቲንግ አቅም ወሳኝነት እንዳላቸው አብራርተዋል።ይህም ለአፍሪካ ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ነው ብለዋል። በዘመናዊው ዓለም የኃይል ሚዛን የሚወሰነው በፈጠራ ባለቤትነት፣ በዳታ ቁጥጥር በተቀመጡ ደረጃዎች መሆኑንም አስረድተዋል። ደረጃዎችን ማውጣት ለቴክኖሎጂ ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ዘርፍ መሆን አለበት ያሉት ፕሮፌሰሯ፣ ኢትዮጵያ እነዚህን ደረጃዎች በፈጠራ ባለቤትነት በማስጠበቅ በዓለም መድረክ ተጽዕኖ ፈጣሪ መሆን እንደምትችል ጠቁመዋል። በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት እያከናወነ ያለውን ስራ በማጠናከር የአፍሪካን ድምፅ የሚያስተጋባ ይሆናል ብለዋል።   በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፐብሊክ ዲፕሎማሲ ባለሙያ ባቻክ ኡጁሉ ኦማን በበኩላችው፣ በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ደረጃ የቴክኖሎጂ ፉክክር ላይ እንገኛለን ብለዋል። ኢትዮጵያ የዓለምን ወቅታዊ እና ነባራዊ ሁኔታ ቀድማ በመገንዘብ የቴክኖሎጂ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የጀመረችው ስራ እጅግ አበረታች መሆኑን ገልጸው፤ በቀጣይም ብዙ የቤት ስራዎች ይጠበቅብናል ነው ያሉት።   በአዲስ አበባ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የፈጠራ ማበልፀጊያ እና የአዕምሮ ጥበቃ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ሀላፊ ፈሊክስ ኢዴሳ፤ መንግስት በተለይም በአፍሪካ የመጀመሪያ የሆነውን የኤአይ ዩኒቨርሲቲ ለማቋቋም እያከናወናቸው ያሉ ተግባራት ቴክኖሎጂን ከውጭ ተቋማት ጥገኝነት ነፃ እንደሚያወጣ ተናግረዋል። ትልቅ የፈጠራ አቀም ላላቸው ኢትዮጵያውያን ወጣቶችም መልካም አጋጣሚ መሆኑንም አንስተዋል።
ኢትዮጵያ በዲጂታል ትስስርና በመሠረተ ልማት አስደናቂ ሥራ እያከናወነች ነው
Feb 24, 2026 131
አዲስ አበባ፤ የካቲት 17/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በዲጂታል ትስስርና በመሠረተ ልማት አስደናቂ ሥራዎችን እያከናወነች መሆኑን በኢትዮጵያ የፊንላንድ አምባሳደር ሲኒካ አንቲላ ገለጹ። አምባሳደር ሲኒካ አንቲላ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያና ፊንላንድ ረጅም ጊዜ ያስቆጠረ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ዲጂታል ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነች ነው ፊንላንድ ከኢትዮጵያ ጋር የትምህርት ዘርፉን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች ጠንካራ የልማት ትብብር እንዳላት ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ፣ በአካባቢ ጥበቃ እና በዲጂታል ትስስር ረገድ ስኬታማ ሥራዎች እየሠራች መሆኑንም አንስተዋል። እንዲሁም በመሠረተ ልማት ግንባታ እያከናወነቻቸው ያሉ ስራዎች የሚደነቁ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ፊንላንድ በአካታች ትምህርት እና በማህበረሰብ አቀፍ የገጠር ውሃ አቅርቦት እንዲሁም የገጠር መሬት ምዝገባን ዲጂታላይዝ የማድረግ ፕሮጀክት ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር እየሠራች እንደምትገኝ ገልጸዋል። አምባሳደሯ አክለውም ከልማት ትብብር ባለፈ የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ የቢዝነስ አጋርነት በመፍጠር ከኢትዮጵያ ጋር ያለንን ዲፕሎማሲያዊ ትብብር ለማጠናከር ቁርጠኛ ነን ብለዋል።
በክልሉ የተጀመረው የኢ- ቲኬቲንግ አገልግሎት ከተሳፋሪዎች የሚነሱ ልዩ ልዩ ቅሬታዎችን በዘላቂነት ይቀርፋል
Feb 24, 2026 93
ዲላ ፤ የካቲት 17/2018(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተጀመረው የኢ- ቲኬቲንግ አገልግሎት ከተሳፋሪዎች የሚነሱ ልዩ ልዩ ቅሬታዎችን በዘላቂነት እንደሚቀርፍ የክልሉ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ አስራ ስድስት ከተሞች ተግባራዊ የሚደረገው የኢ-ትኬት የትራንስፖርት አገልገሎት ዛሬ በዲላ መናኸርያ በይፋ ተጀምሯል። የቢሮው ኃላፊ ተወልደ ተስፋዬ ፤ በክልሉ የተጀመረው የኢ- ቲኬቲንግ አገልግሎት ከተሳፋሪዎች የሚነሱ ልዩ ልዩ ቅሬታዎችን በዘላቂነት እንደሚቀርፍና የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ ድርሻው የጎላ ነው ብለዋል። በክልሉ የመንገድ መሰረተ ልማት ማስፋፋትና አገልግሎቶችን የማዘመን ስራ ላይ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። በተለይ ዲላን ጨምሮ በክልሉ ሶስት ከተሞች ዘመናዊ መናኸሪያዎች ግንባታ ለማከናወን ዝግጅት ከማድረግ ባለፈ አራት የደረቅ ጭነት መናኸሪያዎች ግንባታ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በከተማው ሁሉንም የመንግስት አገልግሎቶች በዲጂታል በማስደገፍ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት በትኩረት እየተሰራ ነው ያሉት ደግሞ የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ መስፍን ደምሴ(ዶ/ር) ናቸው።
የኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት ስትራቴጂ ለትምህርት ሴክተሩ እድገትና ማንሰራራት ጥሩ መሰረት እያኖረ ነው
Feb 24, 2026 160
ወልቂጤ ፤ የካቲት17/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት ስትራቴጂ ለትምህርት ሴክተሩ እድገትና ማንሰራራት ጥሩ መሰረት እያኖረ መሆኑን የወልቂጤ እና የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቁን ተከትሎ፣ በቀጣዮቹ አምስት አመታት የሚተገበር እቅድ ተነድፎ ወደ ስራ መገባቱ ይታወቃል። በዚህም መሰረት በቀጣይ የሚተገበረው የ2030 ስትራቴጂ ባለፉት አምስት ዓመታት ጠንካራ መሰረት የያዘውን የዲጅታል ዘርፍ በማስቀጠል ኢትዮጵያን የዲጂታል ኢንቨስትመንት ማዕከል የማድረግ እንቅስቃሴ በመከናወን ላይ ይገኛል። በእቅዱ መሰረትም ዜጎች ሁሉ በዲጂታል ክህሎት የሰለጠኑ እንዲሆኑ የማድረግ ብሎም የዲጂታል ቴክኖሎጂን በትምህርት፣ በጤና፣ በግብርና፣ በማዕድን፣ በቱሪዝምና ሌሎችም ዘርፎች ዲጂታል ቴክኖሎጂን በስፋት ተግባራዊ ማድረግ ይሆናል። የኢንተርኔትና የኤሌክትሪክ አገልግሎት በሁሉም አካባቢዎች ተደራሽ በማድረግ ለእቅዱ ስኬት ወሳኝ በመሆኑ በዚሁ ልክ ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች ተጀምረዋል። ከዚሁ ጋር በተያያዘ ኢዜአ ያነጋገራቸው የወልቂጤ እና የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን፤ የኢትዮጵያ የዲጅታል ልማት ስትራቴጂ በተለይም ለትምህርት ሴክተሩ እድገትና ማንሰራራት ጥሩ መሰረት እያኖረ መሆኑን ገልጸዋል። በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር ቸርነት ዘርጋ፤ በዲጅታል ልማት ትግበራና ስትራቴጂ ኢትዮጵያ የሚታይ ለውጥና የሚጨበጥ ውጤት ማምጣቷን ተናግረዋል። የዘርፉ ልማት በተለይም ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት እንዲሁም ለምርምር ስራዎች ውጤታማነት ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው አንስተዋል። በዚህ ረገድ በተለየም የዩኒቨርሲቲዎች ሚና ከፍተኛ በመሆኑ የመንግስትን ጥረት በምርምር ጭምር በመደገፍና በማገዝ ለዲጅታል 2030 መሳካት መስራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ አገልግሎት አጋርነት ዳይሬክተር አበበ ሎላሞ (ዶ/ር)፤ በበኩላቸው የዲጅታል አገልግሎት ከትምህርት ተደራሽነት፣ ጥራትና ፈጣን አገልግሎት ለመስጠት የማይተካ ሚና ያለው መሆኑን ገልጸዋል። የጥናትና ምርምር ስራዎችን ለተጠቃሚው ማህበረሰብ በቀላሉ ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም የምርምር ውጤቶችን በመላው ዓለም በቀላሉ ለማስተዋወቅ መልካም እድል ስለመሆኑ አንስተዋል። ኢትዮጵያ በ"ዲጂታል 2025" ስትራቴጂ ባከናወነቻቸው ተግባራት በርካታ ለውጦች መመዝገባቸውን የጠቀሱት ምሁራኑ መንግስት ለሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) እና ለዲጂታል መሰረተ ልማት የሰጠው ትኩረት ለቀጣዩ "ዲጂታል 2030" እቅድ መሳካት ትልቅ ተስፋ የሰነቀ መሆኑን አስረድተዋል።    
በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ያገኘነው እውቀት ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ፈጥሮልናል- ሰልጣኞች
Feb 24, 2026 241
ሆሳዕና ፤ የካቲት 17/2018 (ኢዜአ):- በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ያገኘነው እዉቀት ተጨማሪ ገቢ ለማግኝት አስችሎናል ሲሉ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስልጠናውን የወሰዱ ዜጎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዜጎች የዲጂታል ቴክኖሎጂ ክህሎት እንዲኖራቸው ለማስቻል የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ኮደርስ ስልጠናን በሐምሌ ወር 2016 ዓ.ም ማስጀመራቸው ይታወቃል፡፡ በዚህም በርካታ ወጣቶች አቅማቸውን ለማሳደግ፣ ተጨማሪ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና ዘመኑን የዋጀ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ለመሆን ስልጠናውን በኦን ላይን እየተከታተሉ ናቸው። በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የወሰዱ የመንግስት ሰራተኞች ያገኙት እውቀት ኢኮኖሚያቸውን የሚያሳድጉበትን ተጨማሪ የገቢ ምንጭ በመሆን ተጠቃሚ እያደረገን ነው ይላሉ፡፡ በየም ዞን የሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ ቸርነት ሰውነት ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በመውሰድ ባገኙት እውቀት ተጨማሪ ገቢ ለመፍጠር መቻላቸውን ይገልፃሉ። በዚህም ከመደበኛ የመንግሥት ስራቸው ጎን ለጎን ሶፍትዌሮችን ከማበልፀግ ጀምሮ የተለያዩ ስራዎችን በኦን ላይ በመስራት ከ365 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘት ስለመቻላቸውም ተናግረዋል፡፡ በዚሁ ዞን የባህልና ቱሪዝም መምሪያ ባለሙያ አቶ ምስጋና ከበደ በበኩላቸው በስልጠናው ድረ ገፆችንና የሞባይል መተግበሪያዎችን በማልማት፤ መረጃዎችን የማደራጀት፤ የመተንተንና የተለያዩ ማሽኖችን በመጠቀም የተለያዩ ስራዎችን መስራት እንደሚቻል በቂ ግንዛቤ አግኝተዋል፡፡ የዋቸሞ ዩኒቨርስቲ የኮምፒውተር ሳይንስ መምህርት ፀጋነሽ ሞገስ እና የሶፍትዌር ኢንጂነሪነግ መምሕር የሆኑት አቶ መሳይ አስቻለው፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከዚህ ቀደም በዘርፉ የነበራቸውን ግንዛቤ ከማሳደግ ባለፈ አለማቀፍ ተወዳዳሪነታቸውን ከፍ ለማድረግ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። በዚህም በዘርፉ የሚያሰለጥኗቸውን ተማሪዎች ለዓለም አቀፍ ገበያው በሚመጥን መልኩ ብቁ ለማድረግ ምቹ ሁኔታን እንደፈጠረላቸው አስረድተዋል፡፡ ስልጠናው የተለያዩ መተግበሪያዎችን አልምተው ተጠቃሚ የሚሆኑበትን ምህዳር እንደፈጠረላቸውም ገልጸዋል። በክልሉ ከ200 ሺህ በላይ ዜጎች ስልጠናውን እየተከታተሉ ሲሆን ከነዚህ ውስጥም ከ157 ሺህ በላይ ዜጎች የእውቅና ሰርተፊኬት ማግኘታቸውን የክልሉ ሳይንስና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ቢሮ መረጃ ያመላክታል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም