ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
የአፍሪካን የብልጽግና ጉዞ እውን ለማድረግ የወጣቶችን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ማጎልበት ይገባል -ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Apr 30, 2025 34
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የአፍሪካን የብልጽግና ጉዞ እውን ለማድረግ የወጣቶችን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳደጉ የስታርት አፕ እና ኢኖቬሽን ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ፡፡ "ኢኖቬሽን አፍሪካ 2025" የአፍሪካ የትምህርት፣ አይ ሲ ቲ እና ክህሎት የሚኒስትሮች ስብሰባ " በ21ኛው ክፍለ ዘመን አፍሪካን ማስተማርና ማብቃት" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው። የትምህርት ሚኒስቴር፣የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአፍሪካን ብሬይን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት አህጉራዊ ጉባኤ ዛሬ ይጠናቀቃል። የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ አፍሪካን በትምህርት፣ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ እንዲሁም በክህሎት ልማትና ሥራ ፈጠራ ለማስተሳሰር ያለመ ነው። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል "ለክህሎት ልማትና አዲስ መወዳደሪያ ለአፍሪካ አፍላቂዎች እና ሥራ ፈጣሪዎች" በሚል መሪ ሀሳብ በሚካሄደው የፓናል ውይይት ላይ ንግግር አድርገዋል። ሚኒስትሯ በመክፈቻ ንግግራቸው፤የኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ በኢንዱስትሪዎች፣ ሲቪል ማህበራት፣ በትምህርት ተቋማት መካከል ትብብር በመፍጠር ክህሎትን ለማሳደግ እና የፖሊሲ ግብዓት ለማሰባሰብ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የሀገር በቀል ኢኮኖሚ እና የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎችን በማድረግ ብልፅግናን ለማረጋገጥ እየሰራች መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለበርካታ ወጣቶች የክህሎት ሥልጠና በመስጠት ሥራ ፈጣሪ እንዲሆኑ መደረጉን ተናግረዋል። በዚህም በኢትዮጵያ ሥራ ፈጣሪ እና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ወጣቶችን ማፍራት የሚያስችል አሰራር ስርዓት ተዘርግቶ ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። የዓለም የሥራ ፈጠራ ገበያ ውድድር የበዛበት መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሯ፤ የወጣቶችን የፈጠራ አቅም ማጎልበትና ማበረታታት ይጠበቅብናል ብለዋል። በእያንዳንዱ የቴክኒክ እና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት የክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከላትን በማስፋፋት ለወጣቶች ሥራ ፈጠራ ምቹ ሥነ ምህዳር መፍጠር መቻሉንም ገልጸዋል። በአፍሪካ ወጣቶች በስራ ፈጠራ፣ኢኖቬሽን እና ክህሎት ልማት የላቀ ሚና እንዲኖራቸው ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው ተግባር መሆኑን ጠቁመዋል። የሥራ ፈጠራ ለወጣቶች ከእለት ፍጆታ ባለፈ መሆን አለበት ያሉት ሚኒስትሯ፣ አዳዲስ የፈጠራ ክህሎትን ማዳበር ጭምር መሆኑን ተናግረዋል። በአፍሪካ አካታችና ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት በግብርና፣ ማዕድን፣ ቱሪዝም፣ አይ ሲ ቲ ዘርፎች ላይ ክህሎትን ማስታጠቅ እና ማብቃት ይገባል ብለዋል። የበለጸገች አፍሪካን ለመገንባት መተባበር እና የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎን ማሳደግ እንደሚገባም ተናግረዋል። የኮንጎ ሪፐብሊክ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ሚኒስትር ፕሮፌሰር ጊስላን ማጉሳ ኢቦሜ በበኩላቸው ሀገራቸው የወጣቶችን የዲጂታል ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የነደፈችው ስትራቴጂ ውጤት ማምጣቱን ገልጸዋል፡፡ ኮንጎ ሪፐብሊክ በዓመት ከ200 እስከ 300 ሺህ ወጣቶች ኢንተርፕራይዞችን እንዲቀላቀሉ እቅድ ተይዞ ጥሩ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል፡፡ በአፍሪካ የወጣቶች የሥራ እድል ፈጣራ ሀገራቸው የተሻለ ልምድ እንዳላት የገለጹት ሚኒስትሩ፤ በየክልሉ የኢንተርፕራይዞች ፎረም በማካሄድ ወጣቶች እውቀታቸውንና የሀገራቸውን ሀብት እንዲገነዘቡ እናደርጋለን ብለዋል፡፡ በዚህም የዲጂታላይዜሽን ሥራ ፈጠራ ከነበረበት አዝጋሚ ለውጥ በፍጥነት እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ የሶማሊያ ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዩሱፍ ሞሀመድ አዳን ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂን በመጠቀም በወጣቶች ክህሎት በማበልጸግ አስገራዊ ለውጥ አምጥተናል ብለዋል፡፡ የወጣቶችን ተጠቃሚነት ታሳቢ ያደረገ ብሔራዊ የሥራ ፈጠራ ማዕከል በመገንባት ሥልጠናና የዲጂታል ትምህርት መስጠት ጀምረናል ሲሉም አክለዋል። በተለይም ከግሉ ዘርፍ ጋር በመተባበር ወጣቶችን በታዳሽ ሀይል እና በሥራ ፈጠራ ላይ በቂ ግንዛቤ በማስጨበጥ ወደ ስራ ማስገባታቸውን ገልጸዋል፡፡ ከአፍሪካ ልማት ባንክ እና ከሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበርም የገጠር ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ እንቅስቃሴ እየተደረጉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አፍሪካውያን ከአጋር አካላት ጋር የሚኖራቸው ትብብር ከብሔራዊ ጥቅማቸውና ፍላጎታቸው ጋር የተጣጣመ መሆኑን ማረጋገጥ አለባቸው - የትምህርት ሚኒስትር ብርሀኑ ነጋ (ፕ/ር)
Apr 30, 2025 32
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦አፍሪካውያን የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ከአጋር አካላት ጋር የሚኖራቸው ትብብር ከብሔራዊ ጥቅማቸውና ፍላጎታቸው ጋር የተጣጣመ መሆኑን ማረጋገጥ እንዳለባቸው የትምህርት ሚኒስትር ብርሀኑ ነጋ (ፕ/ር) ገለጹ። "በ21ኛው ክፍለ ዘመን አፍሪካን ማስተማርና ማብቃት" በሚል መሪ ሀሳብ ለሶስት ቀናት ሲካሄድ የቆየው ኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ ዛሬ ተጠናቋል። የትምህርት ሚኒስቴር፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአፍሪካን ብሬን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት አህጉራዊ ጉባኤ በአፍሪካውያን በትምህርት፣ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ፣ በስራ ፈጠራ እና ስታርት አፕ ሪፎርም፣ አቅም ግንባታ እና ስትራቴጂካዊ ትብብር መፍጠር በሚችሉባቸው ጉዳዮች መክሯል፡፡ የትምህርት ሚኒስትር ብርሀኑ ነጋ (ፕ/ር) በማጠቃለያ መርሀ ግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ ጉባኤው የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል በመሰረተ ልማትና መምህራን አቅም ግንባታ ላይ ገንቢ ውይይት የተደረገበት ነው። በጉባኤው ላይ የተነሱ ሀሳቦች የመምህራንን አቅም ለመገንባትና የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ለማሻሻል ሊኖር ስለሚገባው ትብብር መፍትሔ የሚያስቀምጥ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ትምህርት የሁሉም ነገር ቁልፍ መሆኑን ገልጸው፤ በመደበኛ ትምህርት ጥራትና ተደራሽነት ላይ በትኩረት መስራት ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል በትምህርት መሰረተ ልማት እና መምህራን አቅም ግንባታ ተጨባጭ ስራ ጀምራለች ብለዋል። የትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል እና የመምህራንን አቅም በመገንባት የትምህርት ጥራትን ማረጋገጥ የሚያስችል እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ በአፍሪካ ዘላቂና ጥራት ያለው የልጆች ትምህርት ስርዓት ለመገንባት አቅም ግንባታ፣ ዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ የአጭርና ረጅም ዘመን እቅድ ሊኖር እንደሚገባ ገልጸዋል። አፍሪካ በተለዋዋጭ ዓለም ውስጥ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ በመገንዘብ ከሁኔታዎች ጋር መራመድ ካልቻለች የከፋ ነገር ሊገጥማት እንደሚችል ነው ያብራሩት። ዘመኑን የዋጀ ዝግጅት በማድረግ ለቀጣዩ ትውልድ የተመቸች አፍሪካን እውን ማድረግ እንደሚገባም ተናግረዋል። አፍሪካውያን ከአጋር ተቋማት ጋር ያላቸው ትብብር መጠናከር ያለበት ቢሆንም፤ ከአህጉሪቷ ብሔራዊ ጥቅም አኳያ መቃኘት እንዳለበት አስረድተዋል፡፡
በክልሉ በ“ትምህርት ለትውልድ“ ንቅናቄ ውጤት መመዝገቡ ተገለፀ
Apr 30, 2025 43
ደሴ፤ ሚያዚያ 22/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በ“ትምህርት ለትውልድ“ ንቅናቄ ውጤት መመዝገብ መቻሉን የክልሉ ትምህርት ቢሮ ገለፀ። የክልሉ ትምህርት ቢሮ የ2017 ዓ.ም የዘጠኝ ወራት እቅድ ግምገማ መድረክ በደሴ ከተማ እያካሄደ ነው። በመድረኩ ላይ የተገኙት በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የክልሉ ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር) እንደገለጹት ጽንፈኛው ኃይል ፀረ ትምህርት እንቅስቃሴ በማድረግ የመማር ማስተማሩን ሂደት እያወከው ይገኛል፡፡ ይሁን እንጂ ቢሮው ከህብረተሰቡና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በየደረጃው የ“ትምህርት ለትውልድ“ ንቅናቄ በማካሄድ ተማሪዎች እንዲማሩና የትምህርት ጥራቱ እንዲጠበቅ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡ ከየካቲት 3 እስከ መጋቢት 30/2017 ዓ.ም ብቻ በተደረገ ሦስተኛው ዙር ንቅናቄ በፀጥታ ችግር ተዘግተው የነበሩ 112 ትምህርት ቤቶችን ስራ በማስጀመር ከ89 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ወደ ትምህርት ቤት ማምጣት እንደተቻለ ገልፀዋል፡፡ በዚህም ተማሪዎች ያልተማሩትን ትምህርት በማካካስ ጭምር የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ እንዲችሉ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ ለክልላዊና ሀገር አቀፍ ፈተናዎችም ዝግጅት እየተደረገ በመሆኑ ሁሉም በየደረጃው የትምህርት ዘርፉን በመደገፍ ለውጤት ሊያበቃ ይገባል ሲሉም አመልክተዋል፡፡ የሰሜን ወሎ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰጠ ታደሰ በበኩላቸው፤ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት በ“ትምህርት ለትውልድ“ የንቅናቄ ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል ብለዋል፡፡ በሦስተኛው ዙር የንቅናቄ መድረክ ብቻ ከ20 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ወደ ትምህርት ገበታ መመለስ መቻሉን ጠቁመው፤ አሁን ላይ በተረጋጋ ሁኔታ የመማር ማስተማር ስራውን ማከናወን እንደተቻለም ጠቁመዋል፡፡ ''በየደረጃው ለትምህርት በተሰጠው ትኩረት የመማር ማስተማር ስራው እየተሻሻለ መጥቷል'' ያሉት ደግሞ የደቡብ ወሎ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ አለምነው አበራ ናቸው፡፡ በዞኑ የትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል፣ ግብዓት በማሟላትና በሌሎችም የትምህርት ጥራቱን ለማስጠበቅ እየተሰራ ሲሆን ለክልላዊና ሀገራዊ ፈተናዎችም በስፋት ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡ በክልሉ በዜጎች ላይ እገታና ግድያ በመፈፀም እና የትምህርት ሂደትን በማወክ በመምህራን ላይ በደልና ግፍ እያደረሰ ባለው ፅንፈኛ ቡድን ላይ የተጠናከረ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን የአማራ ክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ እሸቱ የሱፍ (ዶ/ር) መግለፃቸው ይታወሳል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል እየተሰራ ነው
Apr 30, 2025 40
ጂንካ፤ሚያዚያ 22/2017(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከእንስሳት ወደ ሰው የሚተላለፉ እና በአካባቢ ብክለት የሚከሰቱ በሽታዎችን ለመከላከል በቅንጅት እየተሰራ ነው። በክልሉ ''የእንስሳት እና የአካባቢ ጤና በመጠበቅ የማህበረሰቡን ጤና መጠበቅ!" በሚል መሪ ሀሳብ የ''አንድ ጤና'' ፕሮግራም እየተተገበረ ነው። በአንድ ጤና ፕሮግራም የክልሉ ጤና ቢሮ፣የግብርና ቢሮ፣ የደንና አካባቢ ጥበቃ ቢሮ፣የውሃ፣ የማዕድንና ኢነርጂ፣ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በመቀናጀት እየሰሩ ይገኛሉ። በተፈጠረው ቅንጅታዊ አሰራርም ከእንስሳት ወደ ሰው የሚተላለፉ እና በአካባቢ ብክልት ምክንያት የሚከሰቱ ተዛማች በሽታዎችን ለመከላከል በትኩረት እየተሰራ ነው። ይህን ለማስፈጸም በጂንካ ከተማ በተካሄደው የምክክር መድረክ ላይ ንግግር ያደረጉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ እንዳሻው ሽብሩ፤ተላላፊ ከሆኑ በሽታዎች 60 በመቶ የሚሆኑት ከእንስሳት ወደ ሰው የሚተላለፉ መሆናቸውን ተናግረዋል። እነዚህን በሽታዎች ለመከላከል ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት መስራት ወሳኝ መሆኑንም ነው የገለጹት። የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ እና የ''አንድ ጤና'' ፕሮግራም ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር አዲሱ እዮብ እንደገለጹት በክልሉ እየተተገበረ ያለው "የአንድ ጤና" ፕሮግራም በሽታን ቀድሞ ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት ይበልጥ ውጤታማ አድርጎታል። በክልሉ የአንድ ጤና ፕሮግራም ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በርካታ ለውጦች መታየታቸውንም አመልክተዋል። በቅርቡ በደቡብ ኦሞ፣ በጋሞ እና በጎፋ ዞኖች የተከሰተው የእንስሳት በሽታ በሰውና በእንስሳት ላይ የከፋ ጉዳት ሳያስከትል በጥቂት ቀናት ውስጥ መቆጣጠር የተቻለበት ሁኔታ የቅንጅታዊ ስራው ውጤት ማሳያ መሆኑን ጠቅስዋል። ከእንስሳት ወደ ሰው የሚተላለፉ አባ ሰንጋ፣ የእብድ ውሻ በሽታ፣ የበግና ፍየል በሽታ፣ የሀሩራማ ትኩሳት በሽታ እና የአዕዋፋት በሽታ እንደሚገኙበትም ተናግረዋል። በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከእንስሳት ወደ ሰው የሚተላለፈውን በሽታ ለመከላከል ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ እንስሳት የአባ ሰንጋ፤ ከ3 ሺህ 800 በላይ ለሚሆኑ ውሾችም የበሽታ መከላከያ ክትባት መሰጠቱን ገልጸዋል። በቀጣይም "የአንድ ጤና" ፕሮግራምን እስከ ቀበሌ መዋቅር ድረስ በማውረድ ፕሮግራሙን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ይሰራል ብለዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ታረቀኝ ሀብቴ በበኩላቸው እንደገለጹት ቢሮው የአንድ ጤና ፕሮግራም ውጤታማ እንዲሆን ድጋፍ እያደረገ ይገኛል። የእንስሳት የሕክምና መስጫ ተቋማትን ከመገንባት ጀምሮ የህክምና ግብአቶችን በሟሟላት እንዲሁም ለጤና ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና በመስጠት ለፕሮግራሙ ስኬታማነት የበኩሉን ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በቀጣይም ፕሮግራሙን በክልሉ አርብቶ አደር አካባቢዎች ተደራሽ በማድረግ ተዛማች በሽታዎችን ለመከላከል የተጀመረው ጥረት እንደሚጠናክርም ተናግረዋል። በምክክር መድረኩ ላይ ቅንጅታዊ ሥራዎችን የሚያጠናክሩ ስምምነቶች የተደረጉ ሲሆን ጠንካራ የአሰራር ስርአት ለመተግበር እንዲያስችልም የስትሪንግ ኮሚቴ ተቋቁሟል።
በክልሉ ለ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ተማሪዎችን የማብቃት ሥራ እየተከናወነ ነው
Apr 30, 2025 37
ጎንደር፤ ሚያዚያ 22/2017 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል በትምህርት ዘመኑ ለ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና የሚቀመጡ ከ99 ሺህ በላይ ተማሪዎችን የማብቃት ሥራ በርብርብ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የዘጠኝ ወራት የትምህርት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በጎንደር ከተማ ተካሄዷል። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ መኳንንት አደመ እንደተናገሩት፤ በክልሉ እየሰፈነ በመጣው ሠላም በመታገዝ የ12ኛ ክፍል ተፈታኝ ተማሪዎችን ውጤት ለማሻሻልና ለማብቃት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። ተፈታኝ ተማሪዎችን በተሟላ መንገድ ለሀገር አቀፉ ፈተና ለማብቃት እየተደረገ ባለው ክልላዊ ንቅናቄም ህብረተሰቡ፣ አጋር አካላት፣ ወላጆች እንዲሁም የትምህርት አመራሩ የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ለአዳር ጥናት ምቹ ሁኔታን በመፍጠር፣ የማጠናከሪያ ትምህርት በመስጠት፣ ቤተ መጽሃፍትና ቤተ ሙከራዎችን በማደራጀትና በግብዓት በማጠናከር ተማሪዎች የተሟላ ዝግጅት እንዲያደርጉ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን ገልጸዋል፡፡ በክልሉ የተፈጠረውን የጸጥታ ችግር በመቋቋም 3 ሚሊዮን የሚጠጉ መደበኛ ተማሪዎችን በመመዝገብ ወደ ትምህርት ገበታ ማምጣት እንደተቻለም አስረድተዋል፡፡ ''ትምህርት የቀጣይ ትውልድ ግንባታ መሰረት ነው'' ያሉት ምክትል ቢሮ ኃላፊው በቀሪ ወራቶች በትምህርቱ ዘርፍ የታቀዱ ተግባራትን ለማስፈጸም ህብረተሰቡና የትምህርት አመራሩ ርብርብ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ''የትምህርት ጥራትን ሽፋንና ፍትሃዊ ተደራሽነትን በማረጋገጥ ተማሪዎችን ለውጤት ለማብቃት ከተማ አስተዳደሩ በትኩረት እየሰራ ነው'' ያሉት ደግሞ የጎንደር ከተማ ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ስንታየሁ ነጋሽ ናቸው፡፡ በዘንድሮ የትምህርት ዘመን በከተማ አስተዳደሩ በሚገኙ 16 ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ውስጥ ከ3 ሺህ 500 በላይ ለሀገር አቀፍ ፈተና የሚቀመጡ ተማሪዎችን ለማብቃት የሚያስችሉ ተግባራት ተከናውነዋል፡፡ ህብረተሰቡ ለ12ኛ ክፍል ተማሪዎች ለሚሰጠው የማጠናከሪያ ትምህርት የሚውል ከ100 ሺህ ብር በላይ በጥሬ ገንዘብ በማዋጣት ድጋፍ ማበርከቱንም ተናግረዋል፡፡ የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ክንዱ ዘውዱ በበኩላቸው፤ በሀገር አቀፉ የ12ኛ ክፍል ፈተና ላይ የሚቀመጡ ተማሪዎች የተሻለ ውጤት እንዲያስመዘግቡ እገዛ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ በዘንድሮ የትምህርት ዘመንም በ29 ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ከ8 ሺህ በላይ ተማሪዎችን ለማስፈተን የማጠናከሪያ ትምህርትን ጨምሮ የአዳር ትምህርት ፕሮግራሞች ተዘጋጅተው ተማሪዎችን የማብቃት ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ገልፀዋል። ለሁለት ቀናት በሚቆየው የግምገማ መድረክ ላይም የጎንደር ከተማን ጨምሮ ከማዕከላዊ፣ ከሰሜንና ከምእራብ ጎንደር ዞኖች የተውጣጡ ሱፐርቫይዘሮች፣ ርዕሳነ መምህራን፣ አጋር አካላትና የትምህርት አመራሮች ተሳታፊ ናቸው፡፡
በአማራ ክልል ዘንድሮ በተገነቡ የውሃ ተቋማት ከ300 ሺህ በላይ ነዋሪዎች የንፁህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ ሆነዋል
Apr 30, 2025 21
ባህር ዳር፤ሚያዚያ 22/2017(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ዘንድሮ በተገነቡ የውሃ ተቋማት ከ300 ሺህ በላይ ነዋሪዎች የንጹህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ መሆናቸውን የክልሉ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈጻጸምና በተሻሻለው የከተማ ውሃና ፍሳሽ አገልግሎቶች አዋጅና ደንብ ላይ የሚመክር መድረክ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ጥላሁን ሽመልስ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ በክልሉ የንፁህ መጠጥ ውሃ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። ለዚህም ዘንድሮ በ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በጀት አንድ ሺህ 257 አነስተኛ፣ መካከለኛና ከፍተኛ የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች እየተገነቡ መሆናቸውን አስረድተዋል። በመገንባት ላይ ካሉት ፕሮጀክቶችም 866 አነስተኛና መካከለኛ እንዲሁም 15 ከፍተኛ የውሃ ፕሮጀክቶች ግንባታ ሥራ ተጠናቆ ለአገልግሎት መብቃታቸውን ተናግረዋል። በእነዚህ የውሃ ተቋማትም ከ300 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለ የገለጹት አቶ ጥላሁን፣ የክልሉን የንፁህ መጠጥ ውሃ ሽፋን አሁን ካለበት 75 በመቶ በ1 ነጥብ 7 በመቶ ለማሳደግ ተችሏል ብለዋል።
በድሬደዋና ምሥራቅ ሐረርጌ ዞን ለሚገኙ አካል ጉዳተኛ ህፃናት 160 ዊልቸር ድጋፍ ተደረገ
Apr 30, 2025 36
ድሬደዋ፣ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ) በድሬደዋና ምሥራቅ ሐረርጌ ዞን ለሚገኙ አካል ጉዳተኛ ህፃናት 160 ዊልቸር ድጋፍ ተደረገ። የድሬደዋ አስተዳደር የሴቶች፣ ህፃናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሁክሚያ መሐመድ በወቅቱ እንዳሉት፤ ቢሮው ከአጋር ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት በህፃናት ላይ የሚደርሱ ማህበራዊ ችግሮችን ለማቃለል የሚያስችሉ ተግባራት በማከናወን ላይ ይገኛል። ህፃናቱ ያሉባቸውን የምግብ፣ የትምህርት፣ የጤናና ሌሎች ማህበራዊ ችግሮችን በማቃለል ቀጣዩ ህይወታቸው እንዲለመልም እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። ዛሬም ፋውንዴሽኑ ለአካል ጉዳተኞች ያደረገው ድጋፍም የዚሁ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፤ መሰል የበጎ አድራጎት ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። ድጋፉን ያደረገው የፋጡማና ኬኛ ፋውንዴሽን የተባለ ግብረ ሰናይ ድርጅት ፕሬዚዳንት ወይዘሮ ተሬዛ አሜ በበኩላቸው ህፃናት ያሉባቸው ችግሮች የማቃለል ስራ ለመንግሥት ብቻ የሚተው ሳይሆን ሁሉም ካለው ላይ በመለገስ የተሻለ ህይወት እንዲመሩ መደገፍ ይኖርበታል ብለዋል። ፋውንዴሽኑ በ56 ሺህ የአሜሪካ ዶላር የተገዙ ዊልቸሮች ድሬደዋና ምስራቅ ሐረርጌ ዞን ለሚገኙ አካል ጉዳተኛ ህፃናት ማከፋፈል መጀመሩን ገልጸዋል። በስነስርዓቱ ላይ ተገኝተው ድጋፉን ለህፃናቱ የሰጡት የድሬደዋ አስተዳደር ምክርቤት የመንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ ሻኪር አህመድ እና ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች ናቸው።
የመምህራንን አቅም በመገንባት የትምህርት ጥራትን ማረጋገጥ የሚያስችል እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው-ሚኒስትር ብርሀኑ ነጋ (ፕ/ር)
Apr 30, 2025 63
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል እና የመምህራንን አቅም በመገንባት የትምህርት ጥራትን ማረጋገጥ የሚያስችል እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኑን የትምህርት ሚኒስትር ብርሀኑ ነጋ (ፕ/ር) ገለጹ። "በ21ኛው ክፍለ ዘመን አፍሪካን ማስተማርና ማብቃት" በሚል መሪ ሀሳብ ለሶስት ቀናት ሲካሄድ የቆየው ኢኖቬሽን አፍሪካ 2025 ጉባኤ ዛሬ ተጠናቋል። የትምህርት ሚኒስቴር፣የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር እና የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአፍሪካን ብሬይን ጋር በመተባበር ያዘጋጁት አህጉራዊ ጉባኤ በአፍሪካውያን በትምህርት፣ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ፣ በስራ ፈጠራ እና ስታርት አፕ ሪፎርም፣ አቅም ግንባታ እና ስትራቴጂካዊ ትብብር መፍጠር በሚችሉባቸው ጉዳዮች ላይ በመምከር ተጠናቋል። የትምህርት ሚኒስትር ብርሀኑ ነጋ (ፕ/ር) በማጠቃለያ መርሀ ግብሩ ላይ እንዳሉት፤ ጉባኤው የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል በመሰረተ ልማትና መምህራን አቅም ግንባታ ላይ ገንቢ ውይይት የተደረገበት ነው። በጉባኤው ላይ የተነሱ ሀሳቦች የመምህራንን አቅም ለመገንባትና የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ለማሻሻል ጥቅም ላይ መዋል አለባቸው ብለዋል። በአፍሪካ ዘላቂና ጥራት ያለው የልጆች ትምህርት ስርዓት ለመገንባት አቅም ግንባታ፣ዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ የአጭርና ረጅም ዘመን እቅድ ሊኖር እንደሚገባ ገልጸዋል። አፍሪካ በተለዋዋጭ ዓለም ውስጥ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ በመገንዘብ ከሁኔታዎች ጋር መራመድ ካልቻለች የከፋ ነገር ይገጥማታል ብለዋል። በመሆኑም ዘመኑን የዋጀ ዝግጅት በማድረግ ለቀጣዩ ትውልድ የተመቸች አፍሪካን እውን ማድረግ እንደሚገባ ተናግረዋል። ትምህርት የሁሉም ነገር ቁልፍ መሆኑን በመግለጽ፣ በመደበኛ ትምህርት ጥራትና ተደራሽነት ላይ በትኩረት መስራት ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል በትምህርት መሰረተ ልማት እና መምህራን አቅም ግንባታ ተጨባጭ ስራ ጀምራለች ብለዋል። አፍሪካውያን ከአጋር ተቋማት ጋር ያላቸው ትብብር መጠናከር ያለበት ቢሆንም፣ከአህጉሪቱ ብሔራዊ ጥቅም አንፃር መቃኘት አለበት ብለዋል።
ከተማ አስተዳደሩ ለጤና መድህን አገልግሎት ከፍተኛ ድጎማ እያደረገ ይገኛል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 30, 2025 51
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ በተያዘው በጀት ዓመት ለጤና መድህን አገልግሎት 1 ቢሊየን ብር የሚደርስ ድጎማ መደረጉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ጉባኤውን አካሂዷል። በጉባዔው ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና የከተማ አስተዳደሩ የስራ ኃላፊዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ የጤና መድህን አገልግሎትን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ አገልግሎቱ ለበርካታ ዜጎች እፎይታ እየሰጠ ቢሆንም በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን መፍታት እንደሚያስፈልግ አንስተዋል። ከንቲባዋ በተያዘው በጀት አመት አስተዳደሩ ለጤና መድህን አገልግሎት 1 ቢሊየን ብር የሚደርስ ድጎማ ማድረጉን ተናግረዋል። በቀጣይም ከጤና መድህን አገልግሎት ጋር ተያይዞ የሚስተዋሉ ተግዳሮቶችን ለይቶ ለመፍታት እንደሚሰራ ገልጸዋል።
ተደራጅተን የአካባቢያችንን ሰላም ማፅናት መቻላችን ልማት ሳይስተጓጎል ማስቀጠላችን ተጠቃሚ አድርጎናል - የጎንደር ነዋሪዎች
Apr 30, 2025 57
ጎንደር፤ ሚያዚያ 22/2017(ኢዜአ)፡- ተደራጅተን የአካባቢያችንን ሰላም ማፅናት መቻላችን የትምህርትና የግብርና ተግባርን ጨምሮ ሌላውም ልማት ሳይስተጓጎል በማስቀጠል ተጠቃሚ አድርጎናል ሲሉ የጎንደር ከተማ ገጠር ቀበሌ ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ ህዝቡ በባለቤትነት ስሜት የአካባቢውን ሰላም ለማረጋገጥ እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ ለጸጥታ መዋቅሩ ተጨማሪ አቅም መሆኑን የጎንደር ከተማ አስተዳደር ሰላምና ጸጥታ መምሪያ ገልጿል። በከተማው የሳይና ሳቢያ ገጠር ቀበሌ ነዋሪ አቶ አለሙ ቢያድግልኝ፤ ሰላምን ማፅናትና ልማትን ማስቀጠል የመንግስት ብቻ ሃላፊነት አለመሆኑን በመገንዘብ ለሰላም አጥብቀን በመስራታችን የአካባቢያችንን የተሟላ ሰላም ማረጋገጥ ችለናል ሲሉ ለኢዜአ ተናግረዋል። በዚህም ተደራጅተን የአካባቢችንን ሰላም በማፅናታችን በቀበሌያችን የሚገኘው ትምህርት ቤት ሥራ ሳይስተጓጎል ልጆቻችን ከትምህርት ገበታ እንዳይለዩ ማድረግ ችለናል ነው ያሉት፡፡ ፅንፈኛው ቡድን በመንግስትና የሕዝብ ተቋማት ንብረቶች ላይ ዘረፋና ውድመት እንዳይፈጽም ባደረግነው ጥበቃ የተሟላ የመንግስት አገልግሎት እያገኘን ነው ብለዋል፡፡ ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ ጓዴ አደራጀው፤ ሰላምና ልማት የማይነጣጠሉ መሆናቸውን በመረዳት የአካባቢያቸውን ሰላም በመጠበቅ የግብርና ስራቸውን በተሟላ መንገድ እያካሄዱ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ በመረከብ የመኸር እርሻ ዝግጅት መጀመራቸውን ጠቁመው፤ በበጋው ወቅት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ልማትና የመስኖ ልማት ስራ ማከናወን እንደቻሉም ጠቅሰዋል፡፡ ተደራጅተው ሰላምን ጠብቀው ማፅናት በመቻላቸው በአካባቢያቸው የትምህርት፣ የጤና አገልግሎትና ሌላም የልማት ተግባር ሳይስተጓጎል በመቀጠል ተጠቃሚ እንደሆኑ የተናገሩት ደግሞ አርሶ አደር ፈንታ ገድሉ ናቸው፡፡ ፅንፈኛው ቡድን ትምህርት ቤት ተዘግቶ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ውጪ እንዲሆኑ ሙከራ ቢያደርግም ተደራጅተን ሰላማችን በመጠበቃችን ልጆቻችን ዛሬ ላይ ትምህርታቸውን ተከታትለው ለዓመቱ ፈተና እየተዘጋጁ ናቸው ብለዋል፡፡ የጎንደር ከተማ አስተዳደር ሰላምና ጸጥታ መምሪያ ሃላፊ አቶ አለልኝ አለም በበኩላቸው፤ የከተማውና ዙሪያ የገጠር ቀበሌ ነዋሪዎች በብሎክ በመደራጀት ሰላማቸውን በማረጋገጥ የተጀመሩ ልማቶች እንዳይስተጓጎሉ ማድረግ እንደቻሉ አረጋግጠዋል። ህዝቡ ከጸጥታ መዋቅሩ ጋር በመቀናጀት ፅንፈኛው ቡድን በእገታ ወንጀል በሚያሰማራቸው የጥፋት ተላላኪዎች የከተማውን ሰላም ለማደፍረስ ሙከራ ያደረጉትን በመያዝ ለህግ በማቅረብ ጠንካራ የሰላም የማስከበር ስራዎችን ሰርተዋል ነው ያሉት። ህዝቡ በባለቤትነት ስሜት የአካባቢውን ሰላም ለማረጋገጥ እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ ለጸጥታ መዋቅሩ ተጨማሪ አቅም በመሆኑ ተጠናክሮ እንዲቀጥልም መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
በህፃናት የቀዳማይ ልጅነት አስተዳደግ ላይ የሚታዩ አበረታች ጅምሮች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል
Apr 29, 2025 74
ድሬዳዋ፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ በህፃናት የቀዳማይ ልጅነት አስተዳደግ ላይ የሚታዩ አበረታች ጅምሮች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ የስፖርት እና የማህበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወርቅሰሙ ማሞ አስገነዘቡ። በድሬዳዋ በህፃናት የቀዳማይ ልጅነት አስተዳደግ በተዘጋጀ ጥናት ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት፣ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች በተገኙበት የውይይት መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩም ዕድሜያቸው ከስድስት ዓመት በታች ህፃናት ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችና መፍትሄዎች ላይ ያተኮረ የዳሰሳ ጥናት ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። በመድረኩ የተገኙት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ የስፖርትና የማህበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወርቅሰሙ ማሞ፤ የመድረኩ አላማ የቀዳማይ ልጅነት ዘመን ላይ በጤና፣ በስርዓተ ምግብ፣ በሁለንተናዊ እንክብካቤ፣ በትምህርትና በደህንነታቸው ላይ የተሻለ ግንዛቤ ለመፍጠር የሚያግዝ መሆኑን አንስተዋል። በህፃናት የቀዳማይ ልጅነት አስተዳደግ ላይ እየታዩ ያሉት አበረታች ጅምሮች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል ሲሉም ተናግረዋል። በዚህ ረገድ በአዲስ አበባ አበረታች ጅምሮች መኖራቸውን ጠቅሰው ድሬዳዋ ከተማን ጨምሮ አጠቃላይ ክልሎች ለተሻለ ስራ የተቀናጀ ርብርብ ማድረግ እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር፤ ጥናቱ በልጆች ዕድገትና ትምህርት ላይ ሁለንተናዊ ለውጥ ማምጣት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። የነገ ሀገር ተረካቢ የሆኑ ህፃናት በተሻለ መልኩ እንክብካቤ ተደርጎላቸው እንዲያድጉ ከወዲሁ መስራት የሁሉም ሃላፊነት መሆኑን አንስተዋል። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ፤ በህፃናት የቀዳማይ ልጅነት ዘመን የልጆችን እድገት የተሻለ ለማድረግ በቅንጀት የምንሰራቸው ስራዎች ለሀገር ሁለንተናዊ ዕድገት ትርጉም ያላቸው ናቸው ብለዋል። በሁሉም ረገድ አሁን ላይ ለህፃናት ተገቢውን ትኩረት በመስጠት የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የአፍሪካ የቀዳማይ ልጅነት ልማት ማዕከል ምክትል ስራ አስፈፃሚ ዶክተር መሠረት ዘላለም፤ ማዕከሉ በአዲስ አበባ ከተቋቋመ ጀምሮ በቀዳማይ ልጅነት ላይ ተጨባጭ ውጤቶች መምጣታቸውን አንስተዋል። የአዲስ አበባን ተሞክሮ በማስፋት በሁሉም አካባቢዎች በህፃናት ቀዳማይ የልጅነት አስተዳደግ ላይ የተደመረ ውጤት ለማምጣት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም በጉዳዩ ላይ ከማዕከሉ እንቅስቃሴ ባለፈ ሁሉም ባለድርሻ አካላትና አጠቃላይ ዜጎች የድርሻቸውን አስተዋጽኦ ሊያበረክቱ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
ለባህርዳር ከተማ ሰላም መጠበቅ የነቃ ተሳትፏችንን እናጠናክራለን - የከተማዋ ነዋሪዎች
Apr 29, 2025 59
ባህርዳር ፤ ሚያዚያ 21/2017(ኢዜአ)፦ ለባህርዳር ከተማ ሰላም መረጋገጥ በባለቤትነት እያደረግነው ያለው ትብብርና ተሳትፎ ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ። በከተማ አስተዳደሩ በሚገኙ ቀበሌዎች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተሳተፉባቸው ህዝባዊ መድረኮች ዛሬ ተካሄደዋል። የመድረኩ ተሳታፊዎችም ለከተማዋ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም መረጋገጥ በባለቤትነት መንፈስ እያከናወኗቸው ያሉ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በከተማው የጣና ክፍለ ከተማ ነዋሪ የሆኑት አቶ ሃብታሙ ገብረእግዚአብሄር፤ የህብረተሰቡ የነቃ ተሳትፎና አንድነት ካለ የማይሳካ ስራ እና እቅድ እንደሌለ አንስተዋል። የባህር ዳር ከተማን ሰላም በማስጠበቅ ረገድ የፀጥታ ሃይሉ ጠንካራ ስራ እንዳለ ቢሆንም የነዋሪውም ተሳትፎና ሚና ታክሎበት የተገኘ ውጤት መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም የከተማዋን ሰላም በፅኑ መሰረት ላይ በማኖር ሁለንተናዊ ልማትና ሀገራዊ እድገትን የማስቀጠል ስራ አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። በተለይም የሰላም ማስጠበቅ ስራ ለአንድ አካል ብቻ የማይተው በመሆኑ በባለቤትነት የምንሰራው የጋራ ጉዳይ ሆኖ ይቀጥላል ሲሉ ተናግረዋል። የሁሉም ነገር መሰረቱ ከምንም በላይ ሰላም በመሆኑ ከመንግስትና ከፀጥታ አካላት ጎን በመሰለፍ የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉም አረጋግጠዋል። ሌላኛው የከተማው ነዋሪ ቄስ ገብረመድህን አምሳሉ፤ የእምነት ተቋማትና የኃይማኖት አባቶች የመጀመሪያ ተግባር ለሰው ልጆች ሰላምን መሻት መልካምነትን ማብዛት መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም ለሀገር ሰላም እና ለህዝቦች አብሮነት መጠናከር ኃላፊነታችንን ለመወጣት ዝግጁ መሆን አለብን ብለዋል። ከዚህም ባለፈ በተለይም ወላጆች ልጆችን የመምከርና ከጥፋት እንዲርቁ የማድረግ ኃላፊነት አለባችው ሲሉም መክረዋል። ሌላኛው የመድረኩ ተሳታፊ አቶ አበጀ አበበ፤ በባህር ዳር ከተማ ሰላምን ከማረጋገጥ በተጓዳኝ በልማት ስራዎች ለተከናወኑት ተግባራት አድናቆታቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም የልማት ስራዎች ከግብ ደርሰው ባህርዳር ለነዋሪዎቿ እና ለቱሪስቶች ምቹና ተመራጭ ሆና እንድትቀጥል ሰላማችንን ማፅናት ይጠበቅብናል ብለዋል። በጣና ክፍለ ከተማ የተካሄደውን ህዝባዊ የውይይት መድረክ የመሩት የከተማ አስተዳደሩ የደንብ ማስከበር መምሪያ ኃላፊ አቶ ኃይለሚካኤል አርዓያ፤ የህዝባዊ ውይይቱ ዓላማ እየተሻሻለ የመጣውን ሰላም ለማጽናት መሆኑን አንስተዋል። የከተማዋ ነዋሪዎች ከፀጥታ ኃይሉ ጋር በቅርበት በመስራት ወንጀለኞችን በማጋለጥና በፅንፈኝነት የሚንቀሳቀሱ አካላትን በመቆጣጠር በከተማዋ ሰላም እንዲሰፍን አስተዋፅኦ አድርገዋል ብለዋል። በከተማ አስተዳደሩ ስር በሚገኙ ቀበሌዎችም ተመሳሳይ የህዝብ መድረኮችን በማካሄድ ሰላምን የማስጠበቅ ጉዳይ የጋራ ስራ ሆኖ እንዲቀጥል መግባባት ላይ ተደርሷል።
የቦሩ ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል ነፃ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ቀዶ ሕክምና አገልግሎት እየሰጠ ነው
Apr 29, 2025 69
ደሴ፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ በደሴ ከተማ የሚገኘው የቦሩ ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል የዓይን ሞራ ግርዶሽ ላለባቸው ሰዎች ነፃ የቀዶ ሕክምና አገልግሎት በዘመቻ እየሰጠ መሆኑን አስታወቀ። የሆስፒታሉ ሥራ አስኪያጅ ተወካይ አቶ ዳዊት ሁሴን እንደገለጹት ሆስፒታሉ ለአንድ ሳምንት በሚቆየው የነፃ ቀዶ ህክምና አገልግሎቱ ከሁለት ሺህ በላይ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ያለባቸው ሰዎችን ለማከም ማቀዱን ጠቁመዋል። በዚህም አገልግሎቱ በደቡብ ወሎ፣ በሰሜን ወሎ፣ በዋግኽምራ ብሔረሰብ፣ በኦሮሞ ብሔረሰብ፣ በሰሜን ሸዋ ዞኖችና ከአፋር ክልል ለሚመጡ ህክምና ፈላጊዎችን ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል። በአገልግሎቱ ነጻ የዓይን ቆብ ቀዶ ህክምና ከመስጠት ባሻገር ለመታከም ለሚመጡ ተገልጋዮች የትራንስፖርትና የምግብ ወጪዎች እንደሚሸፈንላቸው ጠቁመው ለእያንዳንዱ ታካሚ ከ15 ሺህ ብር በላይ በጀት እንደተያዘም ተናግረዋል። የቦሩ ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል የዓይን ሕክምና ክፍል ሃላፊና የነጻ ህክምና አገልግሎቱ አስተባባሪ አቶ እንዳልክ ያረጋል በበኩላቸው አብዛኛውን ጊዜ የዓይን ሞራ ግርዶሽ በዕድሜ መግፋት የሚከሰት ነው ብለዋል። ሕክምናው ኪዩር ብላይንድነስ ፕሮጀክት ከተሰኘ ድርጅት ጋር በመተባበር እየተሰጠ መሆኑን ጠቁመው ከሁለት ሺህ የሚበልጡ ሰዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ መጀመሩን ገልፀዋል። የነጻ ቀዶ ህክምና አገልግሎቱ በተጀመረበት ዕለትም 366 ታካሚዎችን ማስተናገድ መቻሉን ገልጸው በዛሬው ዕለት ደግሞ ከ400 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች አገልግሎቱ ይሰጣል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስረድተዋል። በህክምናው የሆስፒታሉ ስምንት የዘርፉ ስፔሻሊስት ዶክተሮችን ጨምሮ 120 የዓይን ሐኪሞችና ድጋፍ ሰጪ ባለሙያዎች እየተሳተፉ እንደሚገኙ አመልክተዋል። የቦሩ ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል ባለፉት ዓመታት ከ22ሺህ ለሚበልጡ ሰዎች የዓይን ሞራ ቀዶ ሕክምና አገልግሎት መስጠቱን ከሆስፒታሉ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የእንስሳት ጤና እና ደህንነት አዋጅ በዘርፉ የተያዘውን ግብ ማሳካት የሚያስችል ነው
Apr 29, 2025 67
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፡- የእንስሳት ጤና እና ደህንነት አዋጅ በሀገሪቱ በዘርፉ የተያዘውን ግብ ማሳካት የሚያስችል መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 27ኛ መደበኛ ስብሰባ የእንስሳት ጤና እና ደህንነት ረቂቅ አዋጅ ላይ ተወያይቶ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ላሌ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ረቂቅ አዋጁ እየተንሰራፋ የመጣውን ከሰው ወደ እንስሳ እና ከእንስሳ ወደ ሰው ተላላፊ የሆኑ በሽታዎችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚያስችሉ ድንጋጌዎችን የያዘ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም ወደ አገር የሚገቡትንም ሆነ የሚወጡትን እንስሳት እና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርት የዓለም አቀፉን የእንስሳት ጤና ድርጅት አሰራርና ሕግ በተከተለ መልኩ እንዲሆን የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም ለኢኮኖሚው የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ ከፍ በማድረግ የባለሞያዎችን እውቀትና ክህሎት በማጎልበት ተጠያቂነትን በተላበሰ ሁኔታ እንዲንቀሳቀሱ ሥርዓት የሚያስቀምጥ መሆኑን አንስተዋል። ወቅቱን የጠበቀ ዓለም አቀፋዊ እና አህጉራዊ ነባራዊ ሁኔታዎችን የዳሰሰ የሕግ ማዕቀፍ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በወቅቱ እንዳሉት አዋጁ የዘርፉን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። በአዋጁ የተቀመጡ የቅጣት ድንጋጌዎች አስተማሪ መሆን እንዳለባቸው እና የቅጣት እርከኖቹን በተመለከተ ማብራሪያ ጠይቀዋል። ለቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽ እና ማብራሪያ የሰጡት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ላሌ አዋጁ የህግ ክፍተት እንዳይኖረው ተደርጎ መዘጋጀቱን ገልጸው፤ ለዘርፉ ተወዳዳሪነት እና ውጤታማነት ወሳኝ መሆኑን አመላክተዋል። የእንስሳት ጤና እና ደህንነት አዋጅ በዘርፉ እንደሀገር የተያዘውን ግብ ማሳካት የሚያስችል መሆኑን አመላክተዋል። ምክርቤቱም የቀረበውን ረቂቅ አዋጅ ከተመለከተ በኋላ በሙሉ ድምጽ አጽድቆታል። ምክር ቤቱ በቀጣይም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ለምክር ቤቱ የተጓደሉ የቋሚ ኮሚቴ አመራሮችን ለመሰየም የሚያስችል የውሳኔ ሀሳብ ያቀረቡ ሲሆን በዚህም ፕሮፌሰር መሀመድ አብዶ እና አቶ መለሰ መና ለአመራርነት ቀርበዋል። የምክር ቤቱ አባላትም የቀረቡት አመራሮች በትምህርት ዝግጅት እንዲሁም ባላቸው የስራ ልምድ ቋሚ ኮሚቴዎቹን በብቃት መምራት እንደሚችሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። በዚህም መሰረት ፕሮፌሰር መሀመድ አብዶን የከተማ መሰረተ ልማት እና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እንዲሁም አቶ መለሰ መናን ደግሞ የመንግስት የልማት ድርጅቶች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አድርጎ በአብላጫ ድምጽ አጽድቋል፡፡
በመከላከያ ሰራዊት የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ አባላት የገንዘብ ድጋፍ በሰቆጣ ከተማ የህዝብ ዲጅታል ቤተ መፃሕፍት ግንባታ ተጀመረ
Apr 29, 2025 54
ሰቆጣ ፤ ሚያዚያ 21/2017(ኢዜአ)፡- በመከላከያ ሰራዊት የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ አባላት የገንዘብ ድጋፍ በሰቆጣ ከተማ የህዝብ ዲጅታል ቤተ መፃሕፍት ግንባታ መጀመሩን የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ገለጸ። የዕዙ አባላት ከዚህ ቀደም በአስተዳደሩ የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ጨምሮ የህዝብ ተጠቃሚነትን የሚያሳድጉ የተለያዩ የልማት ስራዎችን ሲከናውኑ መቆየታቸውንም ታውቋል። የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ተቀዳሚ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኃይሉ ግርማይ፤ በዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ አባላት የገንዘብ ድጋፍ በሰቆጣ ከተማ የህዝብ ዲጅታል ቤተ መፃሕፍት ግንባታ በይፋ መጀመሩን ተናግረዋል። የዕዙ አባላት ቀደም ሲል ከ60 ሚሊዮን ብር በማዋጣት በተለይም የአካባቢው ወጣቶች የዲጅታል ቤተ መጽሃፍት ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማሰብ ለዚህ ዓላማ መነሳሳታቸውን አስታውሰዋል። ጀግናው የሀገር መከላከያ ሰራዊት የሀገርን ዳር ድንበር ከማስከበር ባለፈ የተለያዩ የልማት ስራዎችን በማከናወንና በማገዝ ህዝባዊነቱን በተግባር የሚያሳይ መሆኑን አንስተዋል። የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ አባላት ገንዘብ በማዋጣት በሰቆጣ ከተማ የህዝብ ዲጅታል ቤተ መፃሕፍት ግንባታ እንዲከናወን ማድረጋቸውም የዚሁ መልካም ተግባር ማሳያ ነው ብለዋል። የዲጂታል ቤተ መፃሕፍት ግንባታው በስድስት ወራት የሚጠናቀቅ ሲሆን በተያዘለት ጊዜ ለመጨረስ አስተዳደሩ ሌት ተቀን ድጋፍና ክትትል የሚያደርግ መሆኑን አረጋግጠዋል። የሰቆጣ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጌትነት እሸቱ፤ የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ አባላት ሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶች ላይ በመሳተፍ እያኖሩት ላለው አሻራ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። በመሆኑም በዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ አባላት የገንዘብ መዋጮ ግንባታው የተጀመረው ቤተ መፅሃፍት በግንባታ ተቋራጩ በጥራትና በፍጥነት እንዲከናወን የቅርብ ክትትል እናደርጋለን ብለዋል። ግንባታውን የሚያከናውነው የአስፋው ቸኮለ ጠቅላላ ተቋራጭ ስራ አስኪያጅ ኢንጅነር ሃይለማርያም አስፋው፤ የቤተ መፃሕፍቱን ግንባታ በተቀመጠለት ጊዜ ለማጠናቀቅ ሌት ተቀን የሚሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል። በግንባታ ሂደቱም እስከ 300 ለሚሆኑ የአካባቢው ወጣቶች የስራ እድል ከመፍጠር ባለፈ በልምድና እውቀት ሽግግር ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑ ታውቋል። የቤተ መጽሃፍቱ የመሰረት ድንጋይ የዳሉል ማዕከላዊ ዕዝ ከፍተኛ መኮንኖች በተገኙበት የተቀመጠ መሆኑ ታወቋል።
በክልሉ የጤና ተቋማትን አገልግሎት አሰጣጥ ለማዘመን በቴክኖሎጂ የተደገፈ የመረጃ ስርዓትን የመዘርጋቱ ተግባር ይጠናከራል
Apr 29, 2025 58
ደብረ ብርሃን፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የጤና ተቋማትን አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ለማሻሻል በቴክኖሎጂ የተደገፈ የመረጃ ስርዓት የመዘርጋቱ ተግባር በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ ጤና ቢሮ የተዘጋጀ የዘጠኝ ወር እቅድ አፈፃፀም ግምገማና በጤናው ዘርፍ የተሰሩ ስራዎች ጉብኝት በደብረ ብርሃን ከተማ እየተካሄደ ነው። የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱልከሪም መንግስቱ በጉብኝቱ ላይ እንደገለጹት በክልሉ የጤና ተቋማት አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ለማሻሻል በቴክኖሎጂ የተደገፈ የመረጃ ስርዓት የመዘርጋቱ ተግባር በትኩረት እየተከናወነ ነው። በጤናው ዘርፍ ቴክኖሎጂን በማበልጸግና በመጠቀም የሚሰጡ አገልግሎቶችና አሰራሮችን ቀልጣፋ በማድረግ በህብረተሰቡ ዘንድ እርካታ ለመፍጠር እየተሰራ እንደሚገኝም አስረድተዋል። ለውጤታማነቱም በክልል ደረጃ የሚተገበሩ ከወረቀት ንክኪ ነጻ አገልግሎቶችን ጨምሮ አዳዲስ ኢንሼቲቮች መጀመራቸውን አስረድተዋል። አገልግሎቱን ለማዘመን በተሰራው ስራ በ25 ጤና ጣቢያዎች ብቁ ሙያተኞችንና መሳሪያዎችን በማሟላት የቀዶ ህክምና አገልግሎት እንዲሰጥ ማስቻሉን ጠቁመዋል። የህክምና መሳሪያዎች፣ መድኃኒትና ሌሎች ግብዓቶች ላይ የሚስተዋለውን እጥረት በቴክኖሎጂ በመታገዝ የመረጃ ልውውጥ በማድረግ ችግሩ ተለይቶ እንደሚፈታም ተናግረዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት በበኩላቸው በከተማዋ እየተስፋፉ የመጡትን የኢንዱስትሪ፣ የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ዘርፎችን የሚመጥን ጽዱ፣ ውብና ምቹ የጤና ተቋማትን ለመፍጠር መድረኩ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል።
ኮሚሽኑ አለመግባባቶችን ወደ ውይይት በማምጣት በዘላቂነት ለመፍታት በሚያደርገው እንቅስቃሴ ማህበሩ የበኩሉን ሚና ይወጣል
Apr 29, 2025 58
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በኢትዮጵያ አለመግባባቶችን ወደ ውይይት በማምጣት በዘላቂነት ለመፍታት በሚያደርገው ጥረት የበኩሉን ሚና እየተወጣ መሆኑን የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አስታወቀ። በኢትዮጵያ የሚታዩ አለመግባባቶችን በምክክርና ውይይት ለመፍታት እንዲቻል ሀገራዊ የሆነ የምክክር ኮሚሽን ተቋቁሞ ወደ ስራ መግባቱ ይታወሳል። ኮሚሽኑም ከተቋቋመ ጀምሮ በኢትዮጵያ መሠረታዊ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የተፈጠሩ አለመግባባቶችን በውይይት ለመፍታት አበክሮ እየሰራ ይገኛል። የኢትዮጵያ መምሕራን ማሕበር ፕሬዚዳንት ዮሐንስ በንቲ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፥ ችግሮችን ለመፍታት ከምክክር እና ውይይት ውጭ መፍትሔ ማምጣት አይቻልም። ማሕበሩ በኢትዮጵያ የማያግባቡ ነገሮችን በውይይትና በምክክር ለመፍታት እየተደረገ ባለው የምክክር ሂደት አጋዥ ለመሆን ከሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጋር ስምምነት መፈራረሙን ገልፀዋል። በዋናነትም ሁሉም አካላት ችግሮችንና የሚያነሷቸውን ጥያቄዎች በውይይት፣በምክክርና በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ለማድረግ ያላሰለሰ ጥረት ያስፈልጋል ነው ያሉት። በኢትዮጵያ ላለፉት በርካታ ዓመታት ችግሮችን በጠበንጃ አፈሙዝ ለመፍታት ጥረት ሲደረግ የቆየ ቢሆንም መፍትሔ ሊያመጣ አለመቻሉ በተጨባጭ መታየቱንም አመልክተዋል። በመሆኑም አለመግባባቶችን በዘላቂነት ለመፍታት ከጠመንጃ አፈሙዝ ይልቅ ውይይትና ምክክርን ማስቀደም እንደሚገባ ጠቅሰዋል። ሁሉም አካላት ለምክክሩ ስኬት የበኩሉን አስተዋጽኦ በማድረግ በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ማገዝ እንደሚጠበቅበትም ፕሬዚዳንቱ ጠቁመዋል። ማህበሩ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ በኢትዮጵያ አለመግባባቶችን ወደ ውይይት በማምጣት በዘላቂነት ለመፍታት በሚያደርገው ጥረት የበኩሉን ሚና እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህ ደግሞ በሁሉም ክልሎች ከወረዳ ጀምሮ ያሉ አባላት ለምክክሩ ስኬታማነት በትብብር እየሰሩ ነው ብለዋል። ምክክሩ ለኢትዮጵያ አስፈላጊና ጠቃሚ መሆኑን ማሕበሩ ያምናል ያሉት ፕሬዚዳንቱ በመምሕራን መዋቅር መሰረትም አጀንዳ በመለየትም ለኮሚሽኑ ያቀረበ መሆኑን ጠቁመዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከእሳትና ሌሎች ድንገተኛ አደጋዎች ከ10 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር በላይ የሚገመት ንብረት ማዳን ተችሏል
Apr 29, 2025 76
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከደረሱ የእሳት እና ሌሎች ድንገተኛ አደጋዎች ከ10 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር በላይ የሚገመት ንብረት ማዳን መቻሉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እሳትና ድንገተኛ አደጋ ስራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ኮማንደር መሐመድ አህመድ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፥ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በአዲስ አበባ እና አካባቢዋ 454 አደጋዎች አጋጥመዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ 303 የሚሆኑት የእሳት አደጋዎች ሲሆኑ ቀሪዎቹ 151 ዱ ደግሞ ድንገተኛ አደጋዎች መሆናቸውን ነው የገለጹት። በደረሱት አደጋዎች ከ 556 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ንብረት ሲወድም የአደጋ ጊዜ ሰራተኞችና ባለድርሻ አካላት ባደረጉት ከፍተኛ ርብርብ ከ10 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር በላይ የሚገመት ንብረት ከውድመት ማዳን መቻሉን ጠቁመዋል። በደረሱት አደጋዎች ህይወታቸዉ አደጋ ውስጥ የነበረ 104 ሰዎችን መታደግ መቻሉንም አስታውቀዋል። ካጋጠሙት አደጋዎች ውስጥ ከፍተኛውን ቁጥር የሚይዘው በመኖሪያ ቤቶች ላይ የተመዘገበው ሲሆን በንግድ ቤቶች ላይ ያጋጠሙ አደጋዎች በሁለተኝነት ተቀምጠዋል። ባለፉት ዘጠኝ ወራት በመዲናዋ እና አካባቢዋ የደረሱ አደጋዎችን በፍጥነት መቆጣጠር በመቻሉ ከፍተኛ ሀብት ከውድመት ማዳን መቻሉን ነው የተናገሩት፡፡ ይህም የኮሚሽኑን አደጋዎችን ፈጥኖ በመቆጣጠር የማዳን አቅሙ 97 በመቶ መድረሱን እንደሚያሳይ አመላክተዋል፡፡ ለአደጋ አጋላጭ የሆኑ መሰረተ ልማቶች በአዲስ መልክ መሰራታቸውን ተከትሎ በከተማዋ የአደጋ ምጣኔ በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ መቻሉን ነው የተናገሩት፡፡ የሚያጋጥሙ አደጋዎችን ለመቆጣጠር እየተደረገ ባለው ጥረት ከኮሚሽኑ እየተላለፉ ያሉ የጥንቃቄ መልዕክቶችን ህብረተሰቡ በአግባቡ መተግበሩ ውጤት ማምጣቱን በመጠቆም ተግባሩን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በድሬደዋ የቀዳማይ ልጅነት ልማት መርሃ ግብርን ተግባራዊ ለማድረግ ያለመ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ነው
Apr 29, 2025 48
ድሬደዋ፣ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦በድሬደዋ አስተዳደር የቀዳማይ ልጅነት ልማት መርሃ ግብርን ተግባራዊ ለማድረግ ያለመ የውይይት መድረክ በመካሄድ ላይ ይገኛል። የመርሃ ግብሩ ዓላማ በቀጣይ አገር ተረካቢ ትውልድ ለመፍጠር በህጻናት ላይ ከወዲሁ መደላድል ለመፍጠር መሆኑም ታውቋል። በመድረኩ ዕድሜያቸው በከተማ አስተዳደሩ ከስድስት ዓመት በታች በሆኑ ህፃናት መሠረታዊ ችግሮች እና መፍትሄዎቻቸውን ያመላከተ የዳሰሳ ጥናት ቀርቦ ውይይት እየተካሄደ ነው። መርሃግብሩ በአዲስአበባ መተግበር የጀመረ ሲሆን በመቀጠል በድሬደዋ እና በሌሎች ከተሞች በመስፋት ላይ የሚገኝ መሆኑም ተገልጿል። በውይይቱ ላይ በህዝብ ተወካዮች ምክርቤት የጤና፣የማህበራዊ ልማትና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ ወርቅሰሙ ማሞ፣ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጄ ዱጉማ፣ የአፍሪካ የቀዳማይ ልጅነት ልማት ማዕከል ዋና ስራ አስፈፃሚ ዶክተር ከበደ ወርቁ፣ እና የድሬደዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃርና ሌሎች የመንግስት የሥራ ሃላፊዎች ተሳታፊ ሆነዋል።
ሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን የጎበኙ የውጭ አገር ቱሪስቶች ቁጥር በእጥፍ ጨምሯል
Apr 29, 2025 61
ጎንደር፤ ሚያዚያ 21/2017(ኢዜአ)፦ የሰሜን ተራሮች ብሄራዊ ፓርክን ባለፉት ዘጠኝ ወራት የጎበኙ የውጭ አገር ቱሪስቶች ቁጥር ከቀደመው በእጥፍ መጨመሩን የፓርኩ ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ የፓርኩ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ማሩ ቢያድግልኝ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ብሄራዊ ፓርኩንና በውስጡ የሚገኙ ብርቅየ እንስሳትን የአካባቢውን ማህበረሰብ በማሳተፍ የመጠበቅ ተግባር እየተከናወነ ይገኛል። በዚህም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ፓርኩን የጎበኙ የውጭ አገር ቱሪስቶች ቁጥር እንዲጨምር ማድረጉን የጠቆሙት ኃላፊው የጎብኚዎቹ ቁጥር ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወራት ጋር ሲነጻጸር በእጥፍ ማደጉን ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ፓርኩን ከተለያዩ የዓለም አገራት የመጡ 2 ሺህ 723 ቱሪስቶች እንደጎበኙት ገልፀዋል። በፓርኩ አዋሳኝ ወረዳዎች በኢኮ ቱሪዝም የተደራጁ ማህበራትም ለቱሪስቶች የመጓጓዣ በቅሎ በማከራየት፣ ጓዝ በመጫን፣ መንገድ በመምራትና ምግብ በማብሰል 3 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ፓርኩ ከቱሪስቶች የመግቢያ ትኬትና ከፊልም ቀረጻ ስራ ደግሞ ግማሽ ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ መሰብሰብ እንደተቻለም ገልፀዋል፡፡ የፓርኩን ብዝሃ ህይወት የበለጠ ለመጠበቅና ብርቅዬ የዱር እንስሳቱን ከህገ-ወጥ አደን ለመታደግ የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ተዘጋጅቶች ወደ ትግበራ መገባቱን አመልክተዋል፡፡ ስትራቴጂክ ዕቅዱ በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኙ የዱር እንስሳትን ህብረተሰቡን በባለቤትነት በማሳተፍ በአስተማማኝ መልኩ ለመጠበቅ የሚያስችል እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ በዚህም በፓርኩ ውስጥ ህገ-ወጥ አደን ፈጽመዋል ተብለው የተጠረጠሩ ሁለት ግለሰቦች በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት መታየት መጀመሩንም ገልፀዋል። የደባርቅ የኢኮ-ቱሪዝም ማህበራት ዩኒየን ስራ አስኪያጅ ቄስ ሞገስ አየነው በበኩላቸው፤ የውጭ አገር ቱሪስቶች ቁጥር መበራከት አባላቱን ከቱሪዝም ገቢ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አስረድተዋል፡፡ ዩኒየኑ 8ሺህ አባላት ያሉት ሲሆን ለቱሪስቶች የመጓጓዣ በቅሎ በማከራየት፣ ጓዝ በመጫን፣ በማጀብና መንገድ በመምራት ከቱሪዝም አገልግሎቱ ተጠቃሚ እየሆኑ ነው ብለዋል፡፡ ፓርኩ በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኙ እንደ ዋልያ፣ ቀይ ቀበሮና ጭላዳ ዝንጀሮን ጨምሮ የሌሎች ብርቅዬ የዱር እንስሳትና አእዋፋት መገኛ ስፍራ ሲሆን 412 ስኩዬር ኪሎ ሜትር ስፋት እንዳለውም ይታወቃል።