ቀጥታ፡
ማህበራዊ
ኢትዮጵያ ለስደተኞች እያደረገች ያለው ድጋፍ ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው
Jan 12, 2026 28
አዲስ አበባ፤ጥር 4 /2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ ድጋፍ በቀነሰበት በአሁኑ ወቅት ለስደተኞች እያደረገች ያለው ድጋፍ ያላትን ጠንካራ የፖለቲካ ቁርጠኝነት እንደሚያመላክት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳዮች ከፍተኛ ኮሚሽነር አስታወቀ። ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለስደተኞች የሚያደርገውን ድጋፍ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳዮች ከፍተኛ ኮሚሽነር (ዩኤንኤችሲአር) የኢትዮጵያ ተወካይ አይሳቱ ንዳዬ፥ ኢትዮጵያ ከአንድ ሚሊዮን ስደተኞች እና ጥገኝነት ፈላጊዎችን ማስጠለሏን ጠቅሰው፥ በተጨማሪም ለተፈናቃይ ዜጎችም ድጋፍ እያደረገች እንደምትገኝ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። የስድተኞች እና ተመላሾች አገልግሎት ተቋማዊ አቅም ለብሄራዊ የስደተኞች ምላሽ ስርዓት ቁልፍ ምሰሶ መሆኑን አመልክተዋል። አገልግሎቱ በስደተኞች ጥበቃ፣ ሰብዓዊ ድጋፍ እና ለተፈናቃይ ዜጎች የረጅም ጊዜ መፍትሄዎችን በማበጀት ቁልፍ ሚና እየተወጣ ይገኛል ብለዋል። ከስደተኞች እና ተፈናቃዮች መካከል ሴቶች እና ህጻናት አብዛኛውን ድርሻ እንደሚይዙ ገልጸው፥ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ድጋፉን እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል። በሌላ በኩል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳዮች ከፍተኛ ኮሚሽነር (ዩኤንኤችሲአር) ከኢትዮጵያ መንግስት፣ከክልል መንግስታት እና ከተቀባይ ማህበረሰቦች ጋር በስደተኞች ጉዳይ ውጤታማ እና የተቀናጀ ምላሽ ለመስጠት በትብብር እየሰራ ነው ያሉት። ዩኤንኤችሲአር ከኢትዮጵያ ጋር ያለው ስትራቴጂካዊ አጋርነት በመተማመን፣ በጋራ ኃላፊነት እና የጋራ ራዕይ ማዕከል ባደረገ መልኩ ዘላቂ መፍትሄ ማምጣት መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ስድተኞችን በመጠበቅ፣መጠልያ በማዘጋጀት፣አስቸኳይ ድጋፎችን በማድረግ፣ ዘላቂ መፍትሄዎችን በመስጠት እና ማህበረሰቦች ለአደጋ የማይበገር አቅም እንዲኖራቸው እያከናወነች ያለውን ስራ አድንቀዋል። ኢትዮጵያ በዓለም ደረጃ ግጭቶች በተበራከቱበት እና የሰብዓዊ እርዳታ እየቀነሰ በመጣበት ወቅት ለስደተኞች በሯን ከፍታ በማስተናገድ ያላትን ጠንካራ የፖለቲካ ቁርጠኝነት እና አመራር ሰጪነት ማሳየቷን ነው የገለጹት። በኢትዮጵያ የዩኤንኤችሲአር ቢሮ መጠልያዎችን ማዘጋጀት እና ዜጎች ራሳቸውን እንዲችሉ ማድረግን ጨምሮ የተለያዩ ድጋፎችን እንደሚያደርግ ጠቁመዋል። ብሄራዊ አቅምን ማጠናከር እና ስደተኞች በዘላቂነት ከማህበረሰቡ ጋር ተቀላቅለው እንዲኖሩ ማድረግ ለስደተኞች እና ለተቀባይ ማህበረሰቦች የጋራ ጠቀሜታን በማስገኘት ረገድ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል። ሁሉንም ስደተኞች እና ተፈናቃዮች አካታች ስራ ለማከናወን የተቀናጀ አሰራርን መከተል እንደሚገባ ነው ንዳዬ ያሳሰቡት። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ጉዳዮች ከፍተኛ ኮሚሽነር (ዩኤንኤችሲአር) እና የኢትዮጵያ መንግስት ከእ.አ.አ 1966 አንስቶ በስደተኞች እና ተፈናቃዮች ጉዳይ ላይ በትብብር እየሰሩ ይገኛሉ።
የህዝቦችን አብሮነትና ወንድማማችነትን የሚያጎለብቱ እሴቶችን በጥናትና ምርምር ማልማትና መጠቀም ይገባል
Jan 11, 2026 74
ሲዝ፣ ጥር 3/2018 (ኢዜአ)፡- የህዝቦችን አብሮነትና ወንድማማችነትን የሚያጎለብቱ ባህላዊ እሴቶችን በጥናትና ምርምር ማልማትና መጠቀም እንደሚገባ የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን ገለጹ። የቤንች ዘመን መለወጫ "ቢስት ባር"ን ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀ የፓናል ወይይት በዞኑ ሲዝ ከተማ ተካሄዷል።   በመድረኩ ላይ የዞኑ አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን እንደገለጹት "ቢስት ባር" በቤንቾች መንደር የጋራ ደስታ የሚጎላበት እና የደረሰ አዝመራን ሰብስበው ፈጣሪን የሚያመሰግኑበት ባህላዊ ኩነት ነው፡፡ በዓሉ ዘመን ከመለወጥ ባሻገር የደረሰን እህል ከጎረቤት ጋር በአንድነት በመቅመስ የሚከበር መሆኑ የአብሮነትና የወንድማማችነት እሴቱ ጎልቶ የሚንጸባረቅበት እንደሆነም ገልጸዋል። እነዚህ እሴቶች ለአካባቢውና ለሀገር ልማት መጎልበት ያላቸውን ፋይዳ በጥናትና ምርምር በማስደገፍ ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ ትኩረት ተሰጥቶት እንደሚሠራ አመልክተዋል። የሼይ ቤንች ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ክፍሌ ጎበዜ በበኩላቸው በዓሉ የያዛቸውን ቱባ ባህሎች ከአካባቢው መስህብ ስፍራዎች ጋር በማስተሳሰር የቱሪዝም ሀብት እንዲሆን ለማስቻል ትኩረት ተደርጓል ብለዋል።   ከአባቶቻችን የመጣውን አብሮ ሰርቶ አብሮ የማደግና የመተባበር ልምድ ወጣቱ አውቆት በመተግበር ለሀገር እድገት ሚናውን እንዲወጣ ማስቻል አለብን ሲሉም ገልጸዋል። የ"ቢስት ባር" ፓናል ውይይት ላይ "ኢኮኖሚያዊ ሥርዓትና የቢስት ባር ባህላዊ መሠረቶች" በሚል ርዕስ ጽሑፍ ያቀረቡት ካሳሁን ሙላት(ዶ/ር) በዓሉ ከምርት ጋር የተገናኘ በዓል በመሆኑ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ከፍ እንደሚል ተናግረዋል።   በተለይም ከ"ቢስት ባር" ማግስት ለቀጣዩ ዓመት ሰፊ የግብርና ሥራ ለማከናወን ቤንቾች ወደ ማሳቸው የሚዘምቱበት መሆኑ ዘላቂና አስተማማኝ የምግብ ዋስትናን የሚያረጋገጥ ዕሴቱ ጉልህ እንደሆነ አብራርተዋል። እነዚህን ባህላዊ ሥርዓቶች ከዘመናዊ እውቀት ጋር በማስተሳሰር የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት ማሳደግ ትኩረት የሚሻ ጉዳይ መሆኑን አመልክተዋል። የፓናል ውይይቱ ላይ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ፍቅሬ አማንን ጨምሮ ሌሎች የፌዴራል እና የክልል የሥራ ኃላፊዎች የተገኙ ሲሆን በዓሉ ጥር 4 እና 5 ቀን 2018ዓ.ም በደማቅ ሥነ ሥርዓት በሼይ ቤንች ወረዳና ሚዛን አማን ከተማ ይከበራል።      
በክልሉ ከታችኛው እርከን ጀምሮ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቷል
Jan 11, 2026 126
ባህርዳር፤ ጥር 3/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ከታችኛው የትምህርት እርከን ጀምሮ ጥራት ያለው ትምህርት ተደራሽ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱን በምክትል ርዕሰ መሰተዳድር ማዕረግ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር) ገለፁ። ‎በባህርዳር ከተማ በ28 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባ የመስከረም16 የቅድመ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ዛሬ ተመርቋል።   በምክትል ርዕሰ መሰተዳድር ማዕረግ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት በክልሉ ጥራት ያለው ትምህርት ተደራሽ ለማድረግ ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶችን ማስፋፋት ላይ ግብ ተይዞ እየተሰራ ነው።   ለዚህም በሁሉም ቀበሌዎች አንድ ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ለመገንባት ታቅዶ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ተናገረዋል። ከፓርትነርስ ኢን ኢዱኬሽን ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በባህር ዳር ከተማ በመስከረም 16 1ኛና መካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ውስጥ ደረጃውን የጠበቀ ሞዴል የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ መጠናቀቁ አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል።   ወደፊትም ባለሃብቶችን፣ ህብረተሰቡንና አጋር አካላትን በማስተባበር የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶችን የመገንባቱ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው በበኩላቸው ትምህርት ለአንድ ሀገር ዕድገትና ብልፅግና መሰረት በመሆኑ ልዩ ትኩረት ሰጥተን እየሰራን እንገኛለን ብለዋል።   ‎በዚህም ደረጃቸውን የጠበቁ ትምህርት ቤቶችን በመገንባት ለመማር ማስተማር ስራው ምቹ ሁኔታ የመፍጠሩ ተግባር ተጠናከሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። ‎በባህርዳር ከተማ በ28 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የመስከረም16 ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ለሌሎች ሞዴል ነው ያሉት ደግሞ የከተማ አስተዳደሩ ትምህርት መምሪያ ኃላፊ ሙሏለም አቤ (ዶ/ር) ናቸው። ትምህርት ቤቱ 14 የመማሪያ ክፍሎች፣ የአስተዳደር ቢሮዎችና ሌሎች አገልግሎት መስጫዎች ያሉትና የውስጥ ቁሳቁስ የተሟላለት መሆኑን ተናግረዋል ።   የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቱ 760 ተማሪዎችን ተቀብሎ የማስተናገድ አቅም ያለው መሆኑንም አመልክተዋል። የፓርትነርስ ኢን ኢዱኬሽን ኢትዮጵያ ቦርድ ሰብሳቢ ሚስተር ቴሬንስ ሂላቢ በበኩላቸው በኢትዮጵያ የትምህርትን ተደራሽነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረጉ እንደሚገኙ አስረድተዋል።   በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።  
በሀላባ ዘመን መለወጫ በዓል ያሉትን የአብሮነትና የእርስ በርስ ትስስር እሴቶች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል-ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) 
Jan 11, 2026 158
ቁሊቶ፣ ጥር 3/2018 (ኢዜአ)፡-የሀላባ ዘመን መለወጫ በዓል "ሴራ" ሲከበር ያሉትን የአብሮነት፣ የመረዳዳትና የእርስ በርስ ትስስር እሴቶችን በሚያጠናክር መልኩ መሆን እንዳለበት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ፡፡ "ሴራ በዓላችን በህብረት የመቻል አቅም ማሳያችን" በሚል መሪ ሀሳብ የሀላባ የዘመን መለወጫ በዓል "ሴራ" በተለያዩ ክዋኔዎች ዛሬ በሀላባ ስታዲየም ተከብሯል፡፡   የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በበዓሉ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት በዓሉ ሲከበር ያሉትን የእርስ በርስ ትስስርና የአብሮነት እሴቶችን በሚያጠናክር መልኩ መሆን እንዳለበት ገልጸዋል። የ"ሴራ" በዓል ከልዩነት ይልቅ አብሮነትና እርስ በርስ መደጋገፍን ለማጠናከር የሚያግዙ እሴቶች እንዳሉት ጠቅሰው፣ በዓሉ ከሃላባዎች ባህል፣ ቋንቋና ታሪክ ጋር የተሳሳረ መሆኑንም አመልክተዋል።   የህዝቦችን አብሮነት በማጠናከር የጋራ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ሥራዎች እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶችን ማስቀጠል እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡ በበዓሉ ላይ የተገኙት የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ነፊሳ አልመሀዲ በበኩላቸው በኢትዮጵያ ማህበራዊ ትስስርን ለማጠናከር የሚረዱ በርካታ እሴቶች እንዳሉ አንስተዋል፡፡ የሀላባ የዘመን መለወጫ በዓል "ሴራ" የአብሮነት፣ የመረዳዳትና የመተሳሰብ እሴት ጎልቶ ከሚንፀባረቅባቸው ባህሎች አንደኛው መሆኑን ጠቅሰው፣ የበዓሉ መከበር እነዚህን ማህበራዊ እሴቶች አጠናክሮ ላማስቀጠል ጠቀሜታ አለው ብለዋል።   የቤተሰብ ኃላፊነትንና የሥራ ድርሻን በአግባቡ መወጣት ጭምር የሚያስተምር በመሆኑ ለልማታዊ እንቅስቃሴ አበርክቶው የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል። የበዓሉን እሴቶች ጠብቆ ለትውልድ ለማስተላለፍና ለማጎልበት በሚደረገው ጥረት ሚኒስቴሩ የሚጠበቅበትን ሚና እየተወጣ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ የሀላባ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሙህዲን ሁሴን በበኩላቸው ሀላባ የራሱ የሆነ ቋንቋ፣ ባህልና የተለያዩ ባህላዊ እሴቶች እንዳሉት አንስተዋል። የዘመን መለወጫ "ሴራ" በዓል በታህሳስ ወር መጠናቀቂያ እና በወርሃ ጥር መግቢያ እንደሚከበርም ነው የተናገሩት። በዓሉ በሃላባዎች ዘንድ ከአሮጌው ወደ አዲሱ ዓመት መሸጋገሪያ መሆኑን ጠቁመው፣ ለአቅመ አዳም የደረሱ ወጣቶች ራሳቸውን ለማስተዳደር ወደ ድርብ ኃላፊነት የሚሸጋገሩበት መሆኑንም አመልክተዋል። "ሀላባ ተከባብሮና ተደማምጦ በጋራ ለመልማት የሚረዱ በርካታ እሴቶች አሉት" ያሉት ደግም የበዓሉ ታዳሚ ወይዘሮ አሚና ኢሳ ናቸው፡፡ ከዚህ ውስጥ አንዱ የሆነው የሀላባ ዘመን መለወጫ በዓል የአብሮነት እሴት የሚጎላበት በዓል መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዓሉን ከሌሎች ወንድምና እህት ህዝብች ጋር በአብሮነት በማክበራቸው ደስተኛ መሆናቸውንም ገልጸዋል። በበዓሉ አከባበር ሥነ ስርዓት ላይ ከፌዴራልና ከክልሉ የመጡ ከፍተኛ አመራሮችና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተሳትፈዋል፡፡  
ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በሥርዓተ-ትምህርት በማካተት ለሀብት ፈጠራና ለሀገር ዕድገት የማዋል ቅድመ ዝግጅት ተጀምሯል
Jan 11, 2026 111
አዲስ አበባ፤ጥር 3 / 2018 (ኢዜአ)፦ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በሥርዓተ-ትምህርት በማካተት ለሀብት ፈጠራና ለሀገር ዕድገት የማዋል ቅድመ ዝግጅት መጀመሩን የትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ። የኢትዮጵያዊያን ሀገር በቀል ዕሴቶች፣ ዕውቀቶች፣ ባህሎችና የአኗኗር ዘይቤዎች ለዜጎች አብሮነት፣ ለሀገር ልማትና ዘላቂ ሰላም ግንባታ ወሰን ተሻጋሪ ፋይዳ እንዳላቸው ይጠቀሳል። የዜጎችን ሀገር በቀል ዕውቀቶችና ዕሴቶች ለዘላቂ ልማትና አብሮነት ግንባታ የሚያበረክቱትን ጉልህ አስተዋትኦ በመንከባከብና በማጥናት ለትውልድ ማስተላለፍ እንደሚገባ ይነሳል። የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኮራ ጡሹኔ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ሀገር በቀል ዕውቀቶች የዜጎች የሁለንተናዊ የማንነት መነሻና መሠረት ናቸው። የኢትዮጵያዊያን ዕምቅ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን ለዜጎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማዋል በተበታተነ አግባብ የተደረጉ ጥናቶች የሚፈለገውን ያክል ውጤት እንዳላመጡ ገልጸዋል። የዘርፉ ተመራማሪዎችና ሥራ ፈጣሪዎች በማሳተፍ የኢትዮጵያዊንን ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በተደራጀ ጥናትና ምርምር ለሀገር ዕድገትና ብልጽግና ጥቅም ላይ ለማዋል በትኩረት እንደሚሰራ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን ሀገር በቀል ዕውቀቶች በሥርዓተ ትምህርት ማካተት የሚያስችል ፕሮጀክት በመቅረጽ በተደራጀ ጥናትና ምርምር ሰንዶ በመለየት ለሀገር ዕድገት ለማዋል ወደ ሥራ መገባቱን አንስተዋል። ሀገር በቀል ዕውቀቶችንም ለሥርዓተ ትምህርት፣ ለፖሊሲ፣ ለልማትና ልዩ ልዩ የሀገር ልማት ግብዓትነት ለማዋል የልየታ ውሳኔ ማሳለፍ የሚያስችል ጥናት ለማካሄድ ዝግጅት መጀመሩን አስታውቀዋል። ከፍተኛ የትምህርትና የምርምር ተቋማት ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በሚያጠኑበት ወቅት ማህበረሰቡ የአካባቢ የሀገር በቀል ዕውቀት መረጃዎችን በአግባቡ በመስጠት ተሳትፎ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።   በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የህብረተሰብ ጤና ትምህርት የሀገር በቀል ዕውቀት የመሰነድ ጅማሮ አስተባባሪ ፕሮፌሰር ምርጊሳ ካባ፤ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በመሰነድ በትምህርት ሥርዓቱ ማካተት ለሀገር ዕድገት ወሳኝ ነው ብለዋል። በቀጣይም ሀገር በቀል ዕውቀቶችን በሳይንሳዊ የጥናትና ምርምር ሥርዓት በማበልጸግ ለሀገር ሁለንተናዊ ልማት እንዲውሉ ለማስቻል በትኩረት እንደሚሰሩ ገልጸዋል። በባሕር-ዳር ዩኒቨርሲቲ የሥነ-ህይወት ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ደስታው ዳምጤ (ዶ/ር)፤ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን ጥቅም ላይ ለማዋል የሚደረጉ የምርምር ሥራዎች የኢትዮጵያን የዕውቀት ምንጭነት የሚገልጡ ናቸው ብለዋል።   ለሀገር ዕድገትና ለዜጎች ዘላቂ ሰላም ግንባታ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸውን ሀገር በቀል ዕውቀቶች መለየት የሚያስችል ጥናትና ምርምር እያካሄዱ እንደሚገኝ ተናግረዋል።  
በምዕራብ ጎንደር ዞን በ70 ሚሊዮን ብር ወጪ የመማሪያ ክፍሎች ግንባታና ጥገና ተከናውኗል
Jan 11, 2026 52
ገንዳውኃ፣ ጥር 3/2018(ኢዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን በ70 ሚሊዮን ብር ወጪ የተከናወነው የመማሪያ ክፍሎች ግንባታና ጥገና የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ለማሻሻል ማገዙን የዞኑ ትምህርት መምሪያ አስታወቀ። የዞኑ ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ደሳለኝ አያና ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በዞኑ የትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ በትኩረት እየተሰራ ነው። በዚህም ህብረተሰቡንና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ በተሰራው ስራ የ108 አዳዲስ የመማሪያ ክፍሎች ግንባታና የ264 ክፍሎች ጥገናን ማጠናቀቅ ተችሏል ብለዋል። ለግንባታና ጥገና ስራውም ከህብረተሰቡ ከ22 ሚሊዮን ብር በላይ የተሰበሰበ ሲሆን ቀሪው ከከተማና ወረዳ አስተዳደሮች እንዲሁም ከግብረ ሰናይ ድርጅቶች የተገኘ መሆኑን አስረድተዋል። በአዲስ ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁት የመማሪያ ክፍሎችም ከስድስት ሺህ በላይ ተማሪዎችን ለማስተናገድ የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከመማሪያ ክፍሎቹ በተጨማሪ የመፀዳጃ ቤት፣ የመምህራን መኖሪያ ቤቶችና የአጥር ግንባታ ስራን ማካሄድ መቻሉን ገልጸዋል። በዞኑ የገንዳውኃ ከተማ ትምህርት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ በየነ አዳነ እንዳሉት፤ የትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል። በዚህም በከተማ አስተዳደሩ፣ መንግስታዊ ባልሆኑ ተቋማትና በህብረተሰቡ ተሳትፎ 12 የመማሪያ ክፍሎች ተገንብተው ለአገልግሎት መብቃታቸውን ገልጸዋል። ከመማሪያ ክፍሎች በተጨማሪ የትምህርት ቤት አጥር፣ መፀዳጃና የቤተ ሙከራ ግንባታ መሰራታቸውን ጠቁመው ይሄም የትምህርት ጥራቱን ለማስጠበቅ ያለመ ነው ብለዋል። የትምህርት ቤቶችን ደረጃ በማሻሻል ውጤታማ የመማር ማስተማር ስራ እንዲኖር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በመተማ ከተማ የጉድኝት ሱፐርቫይዘር ፈቃዴ ከፍያለው ናቸው። የመማሪያ ክፍሎች ጥራቱን የጠበቀ ሆነው መገንባታቸውን ጠቁመው በከተማዋ የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤትም በግንባታ ላይ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ 240 የ1ኛ ደረጃና 10 የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንዳሉ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የቱሪዝም መዳረሻዎችን ለልማት ለማዋል የሚያስችሉ ተግባራት በመከናወን ላይ ናቸው
Jan 11, 2026 98
ጭሮ፤ ጥር 3/2018(ኢዜአ)፡-በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ተፈጥሯዊና ታሪካዊ የቱሪዝም መስህቦችን ለልማት ለማዋል የሚያስችሉ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆናቸውን የዞኑ ቱሪዝም ጽህፈት ቤት ገለጸ። በፅህፈት ቤቱ የቱሪዝም መዳረሻዎች ልማት ቡድን መሪ አቶ ሳንዮ አደም ለኢዜአ እንደገለፁት ከክልሉ የኢኮቱሪዝም መዳረሻዎች አንዱ ተደርጎ የተመረጠውን የጨርጨር ሐይቅን ጨምሮ የተፈጥሮ ዋሻዎችንና ሃይማኖታዊ ቅርሶችን በስፋት የማስተዋወቅ ስራ እየተሰራ ነው። እስካሁንም በዞኑ ከ50 በላይ መስህቦች በዋና ዋና የቱሪዝም መዳረሻነት ተለይተው በፅሑፍ መሰነዳቸውን ገልፀው በቀጣይ አልምቶ ለማስተዋወቅ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ጥረት እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል። በተለይም በጥንታዊው የገዳ ስርዓት አርዳ ጅላ የሆነውን የኦዳ ቡልቱም አካባቢ እና የጨርጨር ሀይቅን በቅንጅት ለማልማት እንቅስቃሴዎች መኖራቸውን አመልክተዋል። በዞኑ እየተከናወነ ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር የጨርጨር ሐይቅን ከጥፋት መልሶ እንዲያገግም እና የደን መጠኑ እንዲጨምር ማድረጉን ጠቁመዋል። ይህም የጨርጨር ሐይቅ እና የድንድን ተፈጥሮ ደን ከክልሉ የኢኮቱሪዝም መዳረሻዎች ውስጥ እንዲካተቱ አድርጓል ብለዋል። በጨረጨር ሐይቅ ላይ ዘመናዊ የጀልባ አገልግሎት እንዲጀምር በማድረግ ባለሀብቶች በአገልግሎት ሰጪነት በመሳተፍ ለልማቱ የበኩላቸውን እንዲወጡም ጥረት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። የቦኬ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ መሀመድ ዘይን ጀማል በበኩላቸው በወረዳው ከ400 በላይ አመት ዕድሜ እንዳስቆጠረ የሚነገርለት ጥንታዊ መስጊድ እና የጨርጨር ሀይቅን የመሰረተ ልማት ስራዎች በመገንባት ለቱሪዝም ምቹ የማድረግ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ጊዜ ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ በጀት ከዋና የመኪና መንገድ እስከ ሀይቁ የሚወስደው መንገድ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ እየተገነባ መሆኑን ለአብነት አንስተዋል። ሐይቁን በመጠበቅና በመንከባከብ የአካባቢው ወጣቶች በዓሳ ማስገር ስራ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከ20ሺህ በላይ የዓሳ ጫጩቶችን ከሌላ አካባቢ በማምጣት የማራባት ስራ እየተሰራ መሆኑን አክለዋል።  
የሀላባ የዘመን መለወጫን በዓለም አቀፍ ቅርስነት ለማስመዝገብ ጥናታዊ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው
Jan 10, 2026 101
ቁሊቶ፤ ጥር 2/2018 (ኢዜአ)፡- የሀላባ የዘመን መለወጫ (ሴራ) በዓልን በዓለም አቀፍ ቅርስነት እንዲመዘገብ የሚያግዙ ጥናታዊ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የኢትዮጵያ ቅርስ ባለሥልጣን አስታወቀ። “ሴራ ባህላችን በኅብር የመቻል ዐቅም ማሳያች ነው” በሚል መሪ ሐሳብ በቁሊቶ ከተማ የሀላባ ባህል፣ ቋንቋና ታሪክ ሲምፖዚዬም ተካሂዷል፡፡ የኢትዮጵያ ቅርስ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኤሊያስ ሽኩር በዚሁ ወቅት፤ የሀላባ ሴራ በዓል ከዘመን መለወጫ በዓልነት ባለፈ ማኅበረሰባዊ ትሥሥርን የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል። ባለሥልጣኑ ሀገር በቀል ዕውቀቶች እንዲጠበቁና ለትውልድ እንዲተላለፉ በጥናት የተደገፈ ሠነድ አዘጋጅቷል ብለዋል። የሀላባ የዘመን መለወጫ በዓል በዓለም አቀፍ ቅርስነት እንዲመዘገብ የሚያግዙ ጥናታዊ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አረጋግጠዋል።   የሀላባ ዞን ዋና አሥተዳዳሪ ሙህዲን ሁሴን በበኩላቸው፤ የሴራ በዓል ባህላዊ ይዘቱን ጠብቆ ለተተኪው ትውልድ እንዲተላለፍ ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል።   የሀላባ የዘመን መለወጫ በዓል የመጠያየቅና የመተጋገዝ ዕሴት የሚጠናከርበት መሆኑን የገለጹት የውይይቱ ተሳታፊዎች፤ ይህን ለማስቀጠል መድረኩ ከፍተኛ ሚና ያበረክታል ብለዋል።
ኢትዮጵያን የሜዲካል ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የሚከናወኑ ተግባራት ይጠናከራሉ 
Jan 10, 2026 131
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያን የሜዲካል ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ በዲጂታል የታገዘ ደህንነቱና ፈዋሽነቱ የተረጋገጠ የምግብ፣ መድሀኒትና የጤና አገልግሎት መስጠት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የጤና ሚኒስቴር ገለጸ። በኢትዮጵያ የጤና ቁጥጥር ስርዓትን ማጠናከር የሚያስችል የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ "ጠንካራ የጤና ቁጥጥር ለማይበገር የጤና ሥርዓት" በሚል መሪ ሀሳብ በዓድዋ ድል መታሰቢያ ተካሂዷል፡፡ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ፍሬህይወት አበበ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በጤናው ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤቶች እንደ ሀገር ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ መከላከልን መሰረት ባደረገ የጤና ፖሊሲ የዜጎችን ጤናና ደህንነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ውጤቶችን ማስመዝገቧን ገልጸዋል፡፡   ይህ የጤና ፖሊሲ መከላከልን መሰረት ከማድረግ ባለፈ ጥራቱና ደህንነቱ የተጠበቀ የህክምና አገልግሎት መስጠት እንዲያስችል ተደርጎ ተሻሽሏል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፎች ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የጀመረችውን ጥረት ማሳካት ወሳኝ መሆኑን በማንሳት፤ ጠንካራ የጤና ቁጥጥር ሥርዓት በመዘርጋት ደህንነቱና ፈዋሽነቱ የተረጋገጠ የምግብ፣ የመድሀኒትና የጤና አገልግሎት ተደራሽ እያደረገች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ የተደረጉ የፖሊሲና የአሰራር ማሻሻያዎች የጤና ቁጥጥር ሂደቱን በማዘመን የማይበገር የጤና ሥርዓት መፍጠር የሚያስችሉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ከሶስት ዓመት በፊት የሀገር አቀፍ የመድሀኒት አቅርቦት በሀገር ውስጥ ምርት የሚሸፈነው ስምንት በመቶ ብቻ እንደነበር በማንሳት፤ በአሁኑ ወቀት 60 በመቶ ደርሷል ብለዋል፡፡ የጥራት መንደር ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፎች ዓለም አቀፍ መመዘኛዎች ጥራታቸውን የጠበቁ ምርቶችን ማቅረብ የሚያስችል ተቋም ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታዋ፤ ለሜዲካል ቱሪዝም መሰረት እንደሚጥልም ገልጸዋል፡፡ የሀገር ውስጥ የመድሀኒትና የህክምና መሳሪያዎች አቅርቦት መሻሻል ፈዋሽነቱና ደህንነቱ የተረጋገጠ ህክምና ከመስጠት ባለፈ ለሜዲካል ቱሪዝም የጎላ አበርክቶ ይኖረዋል ብለዋል፡፡   አፍሪካውያን ለውጭ ህክምና አገልግሎት በዓመት እስከ አንድ ቢሊዬን ዶላር እንደሚያወጡ በመጥቀስ፤ ኢትዮጵያ ባለችበት ጂኦ ስትራቴጂ የሜዲካል ቱሪዝም ማዕከል መሆን እንደምትችል ገልጸዋል፡፡ ብዙ የአፍሪካ ሀገራት የኢትዮጵያን አየር መንገድ እንደሚጠቀሙ በማንሳት፤ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የህክምና አገልግሎት በመስጠት የሜዲካል ቱሪዝምን የሚያረጋግጡ ተግባራት ይጠናከራሉ ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያን የሜዲካል ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የተቋማትን ቅንጅታዊ አሰራር ማሳደግና ዲጂታል ስርዓትን ማዘመን እንደሚገባም ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ባለፉት አራት ዓመታት 260 ሺህ የጤና ባለሙያዎች በተለያዩ ዘርፎች በብቃት ሰልጥነው መመረቃቸውን ገልጸው፣ ይህም የጤና ቁጥጥር ስርዓቱን ለማጠናከር ገንቢ ሚና እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ በጤናው ዘርፍ ያለውን ቁጥጥር በማጠናከር የማይበገር የጤና ስርዓት ለመገንባት የዲጂታል ስርዓት ቁልፍ መሳሪያ ሆኖ ይቀጥላል ብለዋል፡፡
የኮሪደር ልማት ሥራዎች ለነዋሪዎች ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል
Jan 10, 2026 118
ይርጋጨፌ፤ ጥር 2/2018 (ኢዜአ)፡- የኮሪደር ልማት ሥራዎች የከተሞችን ገጽታ በመቀየር ለነዋሪዎች ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውን የጌዴኦ ዞን አሥተዳደር ገለጸ። በይርጋጨፌ ከተማ ሁለተኛው ዙር የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራ ዛሬ በይፋ ተጀምሯል።   የጌዴኦ ዞን ዋና አሥተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በዞኑ የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች የከተሞችን ገጽታ በመቀየር እድገታቸውን እያፋጠኑና ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ እያደረጉ ነው። በዞኑ ዲላ፣ ይርጋጨፌና ወናጎን ጨምሮ በአምስት ከተሞች የተከናወነው የኮሪደር ልማት ሥራ የከተሞችን ደረጃ በማሻሻል ተወዳዳሪነታቸውን አሳድጓል ብለዋል።   በተለይም በጽዱ አካባቢ የመኖር ባህልን በማጎልበት ሕብረተሰቡ ለልማቱ ቅድሚያ እንዲሰጥ ማድረጉን አስገንዝበዋል። ዛሬ በይርጋጨፌ የተጀመረው የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራም የከተማዋን ውበትና ጽዳት በእጅጉ የሚያሳድግ መሆኑን አንስተዋል። የወንዝ ዳርቻ ልማቱ የውኃ ብክለትን በመቀነስ ጤናው በተጠበቀ አካባቢ የመኖር ባህልን የሚያጠናክር መሆኑን ጠቅሰው፤ ለልማቱ ስኬት ባለድርሻ አካላት ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል። የሕብረተሰብ ተሳትፎ በተለይም የግል ባለሃብቶች ተሳትፎን በማጠናከር የከተማዋን እድገት ለማፋጠን ርብርብ ማድረግ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።   የኮሪደር ልማት ከተማዋን ምቹ ማድረጉን ያነሱት የይርጋጨፌ ከተማ አሥተዳደር ከንቲባ ብዙአየሁ ታደሠ በበኩላቸው፤ ከተማዋን አቋርጠው የሚያልፉ ሦስት ወንዞች በአግባቡ ባለመያዛቸው ለብክለት መጋለጣቸውን ተናግረዋል። በፌጤ ወንዝ ላይ ዛሬ የተጀመረው ሁለተኛው ዙር የወንዝ ዳርቻ ልማት 750 ሜትር የእግረኛና የሳይክል መንገድ፣ የአረንጓዴ ስፍራና መዝናኛ ቦታዎችን ጨምሮ የተለያዩ መሠረተ ልማቶች ማካተቱንም ጠቅሰዋል። ይህም የወንዙን ብክለት በማስቀረት ለከተማው ተጨማሪ ውበትና እድገት የሚያጎናጸፍ መሆኑን ነው ያስረዱት። ሥራውን በቀጣይ ሥድስት ወራት አጠናቅቆ ለአገልግሎት ለማብቃት ጥረት እንደሚደረግም ነው ያመላከቱት። ሕብረተሰቡ ይዞታውን በማንሳት አጋርነቱን ማሳየቱን አንስተው፤ በልማቱም ተሳትፎውን ማጠናከር እንደሚጠበቅበት አስረድተዋል።   ከከተማው ነዋሪዎች መካከል መላከሰላም ድረስ ታደሠ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ለወንዝ ዳርቻ ልማት ንብረታቸውን ማንሳታቸውን ተናግረው ልማቱ ፈጥኖ እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። የፌጤ ወንዝ በተለያዩ ደረቅና ፈሳሽ ቆሻሻዎች የተበከለ በመሆኑ ለጤና እክል ሲጋለጡ መቆየታቸውን ያነሱት ደግሞ ሌላኛው የከተማው ነዋሪ ታምራት ታደሠ ናቸው። ዛሬ የወንዝ ዳርቻ ልማት ወደ ሥራ መግባቱ ብክለትን በማስቀረት ጽዱ አካባቢን ይፈጥራል ብለዋል።
የህግ ትምህርት ቤቱ የዘርፉን የሰለጠነ የሰው ሃይል ለማሳደግ እያገዘ ነው
Jan 10, 2026 114
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦የአዲሰ አበባ ዩኒቨርሲቲ የህግ ትምህርት ቤት የሰለጠነ የሰው ሃይል በማፍራት በዘርፉ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚደረገውን ጥረት እያገዘ መሆኑን የፍትሕ ሚኒስትር ሀና አርአያ ስላሴ ገለጹ። ዛሬ በዩኒቨርሲቲው የሕግ ትምህርት ቤቱ 62ኛ አመት የምስረታ በዓል ተከብሯል። ሚኒስትሯ በዚህ ወቅት እንዳሉት የሕግ ትምህርት ቤቱ በፍትሕ ስርዓቱ ውስጥ አስፈላጊ እውቀት እና ክህሎት የጨበጡ ተዋናዮችን በማፍራት ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዝ ነው። ዩኒቨርሲቲው ከስድስት አስርት ዓመታት በበለጠ ጉዞው ዳኞች፣ አቃብያነ ህጎችና ጠበቆችን ጨምሮ በዘርፉ ተሳታፊ የሆኑ በርካታ የሰለጠነ የሰው ሃይል በማፍራት የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰዋል። ዩኒቨርስቲውና ምሁራኑ ከፍትህ ሚኒስቴር ጋር በቅንጅት በመስራት የፖሊሲና የሕግ ማሻሻያ ስራዎችን ጨምሮ የሕግ ማርቀቅ ተግባራት ላይም የላቀ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ ነው የገለጹት። በተለይም የህግ ትምህርት ቤቱ ምሁራን ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ጋር በቅንጅት መስራታቸው ጥራት ያላቸው ህጎች እንዲወጡና ተግባራዊ እንዲደረጉ እያገዘ መሆኑንም ነው የገለጹት። በተጨማሪም በተቋሙ የሚሰሩ የዘርፉ ምሩቃን በትምህርት ቤት ያገኙትን እውቀትና ክህሎት በተጨባጭ በስራ ላይ እንዲያውሉ ለማድረግም በትብብር መስራቱ ሰፊ እገዛ ያለው መሆኑን ነው ያነሱት። እንደ ሀገር የሕግ ትምህርት እና የሕግ ምርምር ላይ በቅንጅት መስራት የፍትሕ ስርዓቱን ጠንካራ ለማድረግ ትልቅ አበርክቶ እንዳለው ገልጸዋል።   የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው በሀገሪቱ የፍትሕ ስርዓት እንዲቀረጽና እንዲተገበር በማድረግ ሰፊ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ነው የተናገሩት። በተለይም የሕግ ትምህርትን ለማስፋፋትና በመላው ሃገሪቱ በፍትሕ ስርዓቱ ውስጥ ተቋማት የሚሰጡት አገልግሎት ጥራት እንዲሻሻል ከማድረግ አንፃር ስኬታማ ስራዎችን መስራቱንም አመልክተዋል። ባለፉት 62 ዓመታት ውስጥም 57 ዙር ተማሪዎችን ያስመረቀ ሲሆን ባለሙያዎቹ ከሀገር ውስጥ ባለፈም በውጭ ሀገራት በዘርፉ የተሻለ ተሳትፎ እያደረጉ መሆኑን ገልፀዋል።   በዩኒቨርሲቲው የህግ ትምህርት ቤት ዲን ፕሮፌሰር ሙራዱ አብዶ፤ የሕግ ትምህርት ቤቱ በዘርፉ የሰው ሀይል ከማፍራት በተጨማሪም ለማሕበረሰቡ ነፃ የህግ አገልግሎት በመስጠት ማሕበራዊ ኃላፊነቱን እየተወጣ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በፍትሕ ስርዓቱ ዋና ተዋናይ የሆኑ ጠበቆች፣ዳኞች፣ተመራማሪዎችንና አማካሪዎችን በማፍራት የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልፀዋል። በመርሃ-ግብሩ ላይ የፍትሕ ሚኒስትሯ ሀና አርአያ ስላሴን ጨምሮ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) እንዲሁም የቀድሞ ተማሪዎች ተገኝተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በክልሉ ለእናቶችና ህጻናት ጤና ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ በተከናወኑ ስራዎች ውጤት እየተገኘ ነው
Jan 10, 2026 61
ባህር ዳር፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ለእናቶችና ህጻናት ጤና ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ በተከናወኑ ስራዎች ውጤት እየተገኘ መሆኑን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው "ፈጠራና ዘላቂ ፋይናንስ ለጤናማ እናትነት" በሚል መሪ ሃሳብ በጥር ወር የሚከበረውን የጤናማ እናትነት ወር አስመልክቶ ዛሬ መግለጫ ዛሬ ሰጥቷል። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አበበ ተምትሜ እንደገለጹት ለእናቶችና ህጻናት ጤና ልዩ ትኩረት በመስጠት ጤናማ ትውልድ ለመገንባት እየተሰራ ይገኛል። እስካሁን በተከናወኑ ስራዎችም ውጤት እየተገኘ መሆኑን ጠቅሰው በቀጣይም የጤናማ እናትነት ወርን ምክንያት በማድረግ ሰፊ የማስተማርና ግንዛቤ የመፍጠር ስራ ይሰራል ብለዋል። በቀጣይም የእናቶችንና ህጻናትን ሞት ለመቀነስ ባለሙያዎችን መመደብና አቅማቸውን ማሳደግ፣ የጤና አገልግሎት መስጫ ተቋማትን በግብአት ማሟላትና ማዘመን ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራ ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት በተሰሩ ስራዎች በጤና ተቋማት የሚወልዱ እናቶች ቁጥር 75 በመቶ ማድረስ መቻሉን ጠቁመው ባለፉት ስድስት ወራት ከ305 ሺህ በላይ እናቶች በጤና ተቋማት መውለዳቸውን ለአብነት አንስተዋል። ከህክምና አገልግሎት አንጻርም በክልሉ ከሚገኙ 100 ሆስፒታሎች በተጨማሪ 36 ጤና ጣቢያዎች ለእናቶች የቀዶ ህክምና አገልግሎት መስጠት የሚያስችል አቅም ያላቸው መሆኑን አስገንዝበዋል። በቀጣይም የቀዶ ህክምና አገልግሎቱን ወደ ሁሉም ጤና ጣቢያዎች ለማስፋት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
የሀላባ የዘመን መለወጫ "ሴራ" ሲከበር የፍቅርና አብሮነት እሴትን በማጠናከር ሊሆን ይገባል
Jan 10, 2026 58
ቁሊቶ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ የሀላባ የዘመን መለወጫ "ሴራ" ሲከበር የፍቅርና አብሮነት እሴትን በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ የዞኑ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ መሀመድአሚን መህዲ ተናገሩ። የ2018 የሀላባ የዘመን መለወጫ "ሴራ" በዓል "ሴራ ባህላችን በህብር የመቻል አቅም ማሳያችን ነው" በሚል መሪ ሀሳብ የፌዴራልና የክልል የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም የተለያዩ ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት አውደ ጥናት በቁሊቶ ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡   በመድረኩ የሀላባ ዞን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ መሀመድአሚን መህዲ፤ የሀላባ ሴራ አብሮነትን ማጠናከር፣ ቅራኔዎችን በይቅርታ መፍታት የሚያስችል የዳበረ እሴት መሆኑን ገልጸዋል። የ"ሴራ"በዓል ከአሮጌው ዘመን ወደ አዲስ ዓመት የመሸጋገሪያና ለአቅመ አዳምና ሄዋን የደረሱ ወጣቶች የሚተጫጩበት ስርዓትን የያዘ መሆኑንም አንስተዋል። በዓሉ የተጣሉ የሚታረቁበት፣ የመደገጋፍና የአብሮነት እሴት የሚጠናከርበት፣ መሆኑን ተናግረው በዓሉ ሲከበር ጠብና ጥላቻን በእርቅና ይቅርታ በመሻር የፍቅርና አብሮነት እሴት በማጠናከር ሊሆን ይገባል ብለዋል።   የሀላባ የዘመን መለወጫ በዓል አከባበር እሴቱን ጠብቆ በማስቀጠል ለተተኪው ትውልድ በማስተላለፍ የሀገር ሃብት ማድረግ አስፈላጊ መሆኑንም አጽኖት ሰጥተዋል። በመድረኩ የቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተር ኤሊያስ ሽኩር ጨምሮ ሌሎችም የዴራልና የክልል የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም የዘርፉ ባለሙያዎች ተገኝተዋል።
በኦሮሚያ ክልል ያለውን እምቅ ሃብት በተደመረ አቅም በማልማት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገው ጥረት ውጤት እያመጣ ነው
Jan 10, 2026 83
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ያለውን እምቅ ሃብት በተደመረ አቅም በማልማት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገው ጥረት ውጤት እያመጣ መሆኑን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ አስታወቀ። በኢትዮጵያ በምግብ ራስን ለመቻልና ከድህነት ለመውጣት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር ተግባራዊ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑ ይታወቃል። በዚህም መሰረት ክልሎች ባላቸው የልማት አቅም ወደ ምርታማነት እንዲገቡ ተደርጎ እስካሁን ስምንት ክልሎች የአደጋ ግዜ ምላሽን በራስ አቅም መሸፈን የሚያስችል አቅም መፍጠር ችለዋል። ከእነዚህ ክልሎች መካከል የኦሮሚያ ክልልን እንቅስቃሴ በተመለከተ ኢዜአ የክልሉን ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ሀይሉ አዱኛን አነጋግሯል። አቶ ሃይሉ በማብራሪያቸው በኦሮሚያ ክልል ያለውን እምቅ ሃብት በተደመረ አቅም በማልማት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የሚደረገው ሽግግር ውጤት የመጣበት መሆኑን ገልጸዋል። የክልሉ መንግስት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በሙሉ አቅም መተግበር፣ ቡሳ ጎኖፋን ማጠናከር፣ ባህላዊ ፍርድ ቤቶችን ተግባራዊ ማድረግ እና 'ጋቸና ሲርና' በተሰኘ መዋቅር ህዝቡ የራሱን ሰላምና ጸጥታ መጠበቅ እንዲችል ተደርጓል ብለዋል። በተለይም ከገዳ ስርዓት የሚመነጨውና የኦሮሞ ህዝብ መረዳጃ ስርዓት የሆነውን ቡሳ ጎኖፋ ተግራዊ በማድረግ በራስ አቅም ችግሮችን የመቋቋም ስራ በልዩ ትኩረት እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም ባለፉት ጥቂት ዓመታት አጋጥመው የነበሩ የተፈጥሮም ይሁን ሰው ሰራሽ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመቋቋም ጥረት ተደርጓል ብለዋል። ቡሳ ጎኖፋ የእርስ በርስ መረዳጃ ስርዓት ብቻ ሳይሆን በመንግስት በተያዘው አቅጣጫ መሰረት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለሚደረገው የሽግግር ጉዞ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑ ገልጸዋል። በዚህም በክልሉ ማህበራዊ ድጋፍ የሚሹ ወገኖች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ መምጣቱን አመልክተዋል። የአደጋ ምላሽን በራስ አቅም ለመወጣት በቡሳ ጎኖፋ አማካኝነት በ2017/18 የምርት ዘመን ከ26ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቶ ምርት እየተሰበሰበ ይገኛል ብለዋል። በተመሳሳይ በክልሉ መንግስት ከሚከናወኑ የልማት ስራዎች ጎን ለጎን ህብረተሰቡ በበጎ ፈቃድ ስራዎች እንዲሳተፍ በማድረግ ትልቅ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑንም ተናግረዋል።። የበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ ከአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ጀምሮ በእርስ በርስ መረዳዳትና በመተጋገዝ እንዲሁም በማህበራዊ አገልግሎቶች ላይ በመሳተፍ በኩል ስኬታማ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።። ከዚህ አንጻር ከ2012ዓ.ም ጀምሮ እካሁን ከ20ሺህ በላይ 'ቡኡራ ቦሩ' የተሰኙ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶች በህዝብ ተሳትፎ ተገንብተዋል ብለዋል። በተጨማሪም 59ሺህ በላይ የገጠር መምህራን መኖሪያ ቤቶችን መገንባት መቻሉን ጠቅሰው ህዝቡን የልማት ተሳታፊ ለማድረግ በተከናወነው ስራ ትልቅ ተሞክሮ የተወሰደበት መሆኑንም አስረድተዋል። በሌላ በኩል ህዝቡ በራሱ ባህላዊ እሴት በመዳኘት ፈጣን ፍትህ በማግኘት ግዜውን ልማት ላይ እንዲያውል ባህላዊ ፍርድ ቤቶች እስከ ቀበሌ ድረስ ተዘርግተው ተጨባጭ ውጤት እየመጣ መሆኑን ተናግረዋል።
በጎንደር የጥምቀት በአል በድምቀት እንዲከበር የተሟላ ዝግጅት ተደርጓል
Jan 10, 2026 59
ጎንደር ፤ ጥር 2/2018 (ኢዜአ)፦ በጎንደር የጥምቀት በአል በድምቀት እንዲከበር የተሟላ ዝግጅት መደረጉን የከተማ አስተዳደሩ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ አስታወቀ፡፡ የጥምቀት ስነ-ስርአት የሚካሄድበት የአጼ ፋሲል መዋኛ ስፍራ ታሪካዊ ቅርስነቱን በጠበቀ መልኩ እድሳት ተደርጎለት ለበዓሉ ዝግጁ መሆኑም ታውቋል። የመምሪያው የቅርስ ጥበቃና ቱሪዝም ልማት ቡድን መሪ አይቸው ታደሰ፤ የጥምቀት በአል በጎንደር በርካታ የውጭና የሀገር ውስጥ ጎብኝዎች፣ ምእመናንና ሌሎችም እንግዶች በተገኙበት በድምቀት ለማክበር ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል።   ለበዓሉም ታቦታት ከመንበራቸው ወጥተው የሚያድሩበትና በርካታ የእምነቱ ተከታዮችና ቱሪስቶች የበአሉን መንፈሳዊና ባህላዊ ሁነት የሚከታተሉበትን ቦታ በማደስና በመጠገን ለአገልግሎት ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል። ከ400 ዓመት በላይ እድሜ ያስቆጠረው የጥምቀት ስነ ስርአት የሚካሄድበት የአጼ ፋሲል መዋኛ የተሟላ እድሳት ተደርጎለት ለበዓሉ ዝግጁ መደረጉን ገልጸዋል። የመዋኛ ገንዳው ላይ የውሃ ስርገት እንዳያጋጥም አንድ ሺህ ካሬ ሜትር የጥገና ስራን ጨምሮ ከዚህ በፊት የነበረውን አንድ የመግቢያ በር ወደ ሶስት ማሳደግ የሚያስችሉ የግንባታ ስራዎች ተከናውነዋል ብለዋል፡፡   በመዋኛ ገንዳው የሚሞላውን የጸበል ውሃ በቅርብ ለማግኘት እንዲያስችልም 300 ሜትር ጥልቀት ያለው የውሃ ጉድጓድ ተቆፍሮ ለአገልግሎት ዝግጁ ስለመሆኑ ገልጸዋል። ለእንግዶችና ለቱሪስቶች ማረፊያ የተዘጋጁ የብረት ደረጃና ወንበሮችም የእድሳት ስራ የተከናወነላቸው መሆኑን ገልጸው የመብራት፣ የኢንተርኔትና የመጀመሪያ ደረጃ ህክምና መስጫ ስፍራዎች ተዘጋጅተዋል ብለዋል። የቱሪስቶችን ቆይታ ለማራዘምም ከጥምቀት በአል አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ የባህል ሳምንት ፌስቲቫል፣ የጎዳና ላይ ትርኢቶችና ሌሎች ዝግጅቶች እንደሚካሄዱም ጠቁመዋል።
ጠንካራ የጤና ቁጥጥር ስርዓት በመፍጠር ደህንነቱና ፈዋሽነቱ የተረጋገጠ የምግብ የመድሀኒትና የጤና አገልግሎት እየተሰጠ ነው
Jan 10, 2026 62
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ጠንካራ የጤና ቁጥጥር ስርዓት በመፍጠር ደህንነቱና ፈዋሽነቱ የተረጋገጠ የምግብ የመድሀኒትና የጤና አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ፍሬህይወት አበበ ገለጹ። በኢትዮጵያ የጤና ቁጥጥር ስርዓትን ማጠናከር የሚያስችል የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ "ጠንካራ የጤና ቁጥጥር ለማይበገር የጤና ሥርዓት" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ፍሬህይወት አበበ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በጤናው ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤቶች እንደ ሀገር ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ አንዱ መሳሪያ ነው። ኢትዮጵያ መከላከልን መሰረት ባደረገ የጤና ፖሊሲ በዜጎች ጤናና ደህንነት ላይ አወንታዊ ለውጥ ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል።   ይህ የጤና ፖሊሲ ጥራትና ደህንነቱ የተጠበቀ የህክምና አገልግሎት መስጠት፣ የሀገር ውስጥ ምርት ጥራትና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ማሳደግ በሚያስችል ሁኔታ እንዲሻሻል ተደርጓል ብለዋል። በዚህም ከአራት ዓመት በፊት ስምንት በመቶ ብቻ የነበረውን የሀገር ውስጥ የመድሀኒት አቅርቦት ሽፋን ወደ 60 በመቶ ማሳደግ እንደተቻለ ተናግረዋል። በጤና ፖሊሲ፣ ስትራቴጂና ህጎች ላይ ጠንካራ የጤና ቁጥጥር ሥርዓት በመፍጠር ደህንነቱና ፈዋሽነቱ የተረጋገጠ የምግብ፣ የመድሀኒትና የጤና አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። የሀገር ውስጥ የመድሀኒትና የህክምና መሳሪያዎች አቅርቦት መሻሻል ፈዋሽነቱና ደህንነቱ የተረጋገጠ ህክምና ከመስጠት ባለፈ የውጭ ምንዛሪን በማዳን የጎላ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል። ጠንካራ የጤና ቁጥጥር ስርዓቱ ኢትዮጵያ በሜዲካል ቱሪዝም ተጠቃሚ የምትሆንበትን ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም ጠቁመዋል። በኢትዮጵያ ባለፉት አራት ዓመታት 260ሺህ የጤና ባለሙያዎች በተለያዩ ዘርፎች በብቃት ሰልጥነው መመረቃቸውንና ለጤና ቁጥጥር ስርዓቱን ለማጠናከር ገንቢ ሚና አላቸው ብለዋል። በጤናው ዘርፍ ያለውን ቁጥጥር በማጠናከር የማይበገር የጤና ስርዓት መገንባት እንደሚገባ በማንሳት፣ የተቋማትን ቅንጅታዊ አሰራር ማሳደግና ዲጂታል አሰራርን በሁሉም አካባቢ ተደራሽ ማድረግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
ጉበትን ጤናማ በሆኑ ልምዶች እንዴት መጠበቅ ይቻላል?
Jan 10, 2026 92
ጉበት ከ500 በላይ ሥራዎችን የሚያከናውን ዋነኛ እና ሁለገብ የሰውነታችን አካል ነው ይላሉ በአለርት ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የውስጥ ደዌ ስፔሻሊስት እና የጨጓራ፣ አንጀት እና ጉበት ሰብ ስፔሻሊስት ዶክተር አብዲ ባቲ። የጉበት ተግባራት በአራት ዐቢይ ክፍሎች እንደሚከፈሉም ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ አስረድተዋል። የመጀመሪያው ተግባሩ፤ ጎጂ ንጥረ ነገሮችን ከደም ውስጥ ማጽዳት፣ ቆሻሻ ምርቶችን ማስወገድ፣ የመድኃኒቶችን ሜታቦሊዝም ማከናወን፣ ከምንበላው፣ ከምንጠጣው እና ከምንተነፍሰው ሁሉ መርዞችን ማስወገድ ነው ይላሉ። እንዲሁም ሁለተኛው ተግባሩ፤ ቫይታሚኖችን፣ ማዕድናትን እና ኃይልን ማከማቸት መሆኑን ገልጸው፤ ለሰውነታችን ማበረታቻ ኃይል በሚያስፈልግበት ጊዜ ዝግጁ ማድረግ ነው ብለዋል። ሦስተኛው ተግባር ደግሞ፤ ለደም መርጋት እና ኢንፌክሽኖችን ለመዋጋት ፕሮቲኖችን ማመንጨት መሆኑን ያስረዳሉ። አራተኛው ተግባሩን ሲያብራሩም፤ ‘Bile’ የሚባል ንጥረ ነገር በማምረት ከሚወዷቸው (ከሚመገቧቸው) ምግቦች ውስጥ የሚገኘውን ስብ እንዲፈጭ ያደርጋል ሲሉ ገልጸዋል። ጉበትን ለህመም የሚያጋልጡ መንስኤዎች ምንድን ናቸው? • እንደ ዶክተር አብዲ ገለጻ፤ ጉበት ዘርፈ ብዙ ተግባራት ያለው ወሳኝ የሰውነት አካል እንደመሆኑ ለብዙ አደጋዎች ይጋለጣል። ከነዚህ አጋላጭ ምክንያቶች መካከል ከታቻ የተጠቀሱት ዋነኞቹ ናቸው ብለዋል። እንደ ሄፓታይተስ ቢ እና ሲ ባሉ ቫይረሶች በደም፣ በመርፌ ወይም ወሊድ ወቅት የሚተላለፉ፤ ከመጠን በላይ አልኮል መጠቀም፤ ከመጠን በላይ መወፈር ፤ የስኳር በሽታ፤ ከእፅዋት እና የተለያዩ እህሎች (ለምሳሌ ከማሽላ እና በቆሎ) ውስጥ የሚገኙ እንደ አፍላቶክሲን ያሉ መርዛማ ንጥረ ነገሮች ይገኙበታል ብለዋል። በተጨማሪም ከ40 ዓመት በላይ መሆን፣ በቤተሰብ የሚተላለፉ የጉበት በሽታዎች መኖር፣ የተመጣጠነ ምግብ እጥረት እና አደገኛ ልማዶች ለጉበት በሽታ ከሚያጋልጡ መንስዔዎች መካከል ናቸው ይላሉ። ከእነዚህ አጋላጭ መንስኤዎች አብዛኛዎቹ ሊወገዱ የሚችሉ እንዲሁም ቀድመን በማወቅ እና በመጠንቀቅ መከላከል የሚቻሉ ናቸው ይላሉ የሕክምና ባለሙያው። ጉበትን በቀላል እና ጤናማ በሆኑ ልምዶች እንዴት መጠበቅ ይቻላል? • በየዕለቱ በቂ ንጹህ ውኃ በመጠጣት፤ • ጤናማ አመጋገብ በመከተል (እንደ ፍራፍሬ፣ አትክልት፣ ጤፍ፣ ባቄላ እና ዓሣ በመመገብ)፤ • ከመጠን በላይ ስብን እና ስኳርን በመቀነስ፤ • አካላዊ እንቅስቃሴን በማዘውተር፤ • አልኮልን በመገደብ ወይም በጭራሽ ባለመጠቀም፤ • የሄፓታይተስ ክትባት በመውሰድ፤ • ያልተረጋገጡ እፅዋትን ከመጠቀም በመቆጠብ፤ • መድኃኒት ከመውሰድ በፊት የጤና ባለሙያ በማማከር እንዲሁም የግል እና የምግብ ንጽህናን በመጠበቅ የጉበትን ጤንነት መጠበቅ ይቻላል ብለዋል ዶክተር አብዲ። ሕክምናውን በተመለከተ o ዶክተር አብዲ እንዳሉት፤ አብዛኛዎቹ የጉበት በሽታዎች ሊታከሙ ይችላሉ፤ በጊዜ ከተደረሰም መቆጣጠር እና መዳን ይችላሉ። o ለሄፓታይተስ ቢ/ሲ ፀረ-ቫይረስ መድኃኒቶች ሕክምና መከታተል፤ o አልኮል መጠጣት በማቆም ጉበት በፍጥነት እንዲያገግም ማገዝ፤ o ለሰባ ጉበት፣ ለስኳር በሽታ እና ለኮሌስትሮል መብዛት በመድኃኒት ማከም፤ o አመጋገብን ማስተካከል፣ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ማድረግ፤ o የከፋ ደረጃ ላይ የደረሰ ከሆነ እንደደረጃው የተለያዩ ሕክምናዎች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ እስከ ንቅለ ተከላ ድረስ ሊታከም ይችላል ብለዋል። ጉበት በዓለም አቀፍ ደረጃ…. በዓለም አቀፍ ደረጃ ወደ 2 ቢሊየን የሚጠጉ ሰዎች እንደ ሄፓታይተስ ቢ እና ሲ ያሉ የጉበት ህመሞች ተጋላጭ ናቸው። ለዚህም ከመጠን በላይ አልኮል መጠጣት፣ ውፍረት እና የስኳር በሽታ በሰፊው በዓለም አቀፍ ደረጃ ብዙዎችን ተጋላጭ ያደርጋሉ ነው ያሉት። በአፍሪካ ውስጥ ወደ 80 ሚሊየን የሚጠጉ ሰዎች ለሄፓታይተስ ቢ በሽታ ተጋላጭነት ውስጥ ይኖራሉ። ከዚህ ውስጥ 60 በመቶው የሚሆነው በክትባት ውስንነት፣ በጤና አጠባበቅ ተደራሽነት እና በአፍላቶክሲን የተበከሉ (እንደ በቆሎ እና ማሽላ ባሉ) ሰብሎች ምክንያት ለአደጋ ተጋላጭ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያም እስከ 7 በመቶ ያህሉ ሕዝብ ለሄፓታይተስ ቢ ተጋላጭ መሆኑን ነው ያመላከቱት። ለዚህም አልኮል አላግባብ መጠቀም፣ ጫት መጠቀም እና የስኳር በሽታ መጨመር ለብዙዎች በተለይም ከ40 ዓመት በላይ ለሆኑ ወንዶች ተጋላጭነትን እንደሚጨምር አስገንዝበዋል። በአጠቃላይ ክትባት በመውሰድ፣ ጤናማ የአኗኗር ዘይቤ በመከተል፣ ጤናማ አመጋገብ በማዘውተር ብሎም በወቅቱ በመታከም ተጋላጭነትን በመቀነስ የጉበት ጤንነትን መጠበቅ ይገባል ሲሉ መክረዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የማሌ የዘመን መለወጫ በዓል የእርስ በርስ ትስስርን ለማጠናከር ትልቅ አበርክቶ አለው
Jan 9, 2026 156
ጂንካ፤ ጥር 1/2018(ኢዜአ)፦የማሌ የዘመን መለወጫ በዓል "ዶኦሞ" እሴት የህዝብን የእርስ በርስ ትስስር በማጠናከር ለሀገራዊ አንድነትና ሰላም ትልቅ አበርክቶ እንዳለው ተገለጸ። የማሌ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ "ዶኦሞ" በዓል በደቡብ ኦሞ ዞን ማሌ ወረዳ በሌሞጌንቶ ከተማ በፓናል ውይይት ተከብሯል። የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ፣ "ዶኦሞ" የአንድነት፣ የሰላምና የወንድማማችነት ተምሳሌት መሆኑን ጠቅሰው፣ በዓሉ አብሮነትን በማጠናከር ለሀገራዊ አንድነትና ሰላም ትልቅ አበርክቶ አለው ብለዋል።   የበዓሉ መከበር የማሌዎች ባህላዊ እሴቶችንና ያሏቸውን ታሪካዊ ቅርሶች ለትውልድ ለማስተዋወቅ ትልቅ ፋይዳ እንዳለውም አንስተዋል። በበዓሉ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ አቅናው ካውዛ በበኩላቸው፤ የማሌ የዘመን መለወጫ በዓል "ዶኦሞ" የህዝብን የእርስ በርስ ትስስር፣ አብሮነትና ሰላምን የሚያጠናክሩ እሴቶች አሉት።   የበዓሉን እሴቶች በጥናትና ምርምር ከማሳደግ ባለፈ በዓሉን ለማስተዋወቅ ትኩረት ተሰጥቶት ሊሰራበት እንደሚገባ ተናግረዋል። ማሌዎች የራሳቸው የጊዜ ቀመርና አቆጣጠር እንዳላቸው የተናገሩት ደግሞ የማሌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አልጋጋ ባልንሴ ናቸው፡፡   በዓሉ በየዓመቱ ጥር 1 ቀን ወይም በብሄረሰቡ አጠራር "ባሬ ፔቴ" ተብሎ በሚጠራው ወር የሚከበር ሲሆን፣ በዓሉም ባለፈው ዓመት ለሆነው መልካም ነገር ለፈጣሪ ምስጋና የሚያቀርቡበት ነው። በተጨማሪም መጪው አዲስ ዓመት የሰላም፣ የፍቅር፣ የጤናና የአብሮነት እንዲሆን ፈጣሪን በመማፀን ያከብሩታል። በዛሬው እለትም በዓሉ "የዶኦሞ ብስራት ለአንድነትና ለዕድገት" በሚል መሪ ቃል በፓናል ውይይትና በተለያዩ ባህላዊ ሥርአቶች መከበሩን አመልክተዋል። በክብረ በዓሉ ላይ በየደረጃው ያሉ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም የሀገር ሽማግሌዎችና የእምነት አባቶች መገኘታቸው ታውቋል።
በድሬዳዋ በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የተመዘገቡ የልማትና መልካም አስተዳደር ውጤቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ 
Jan 9, 2026 118
ድሬዳዋ፤ ጥር 1/2018(ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ አስተዳደር በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የተመዘገቡ የልማትና መልካም አስተዳደር ውጤቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአስተዳደሩ ከንቲባ ከድር ጁሃር አስታወቁ። የአስተዳደሩ ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት እና የሴክተር ተቋማት የግማሽ በጀት ዓመት የስራ አፈፃፀም ዛሬ ተገምግሟል። የግምገማውን መድረክ የመሩት የአስተዳደሩ ከንቲባ ከድር ጁሃር በወቅቱ እንዳሉት፤ በግማሽ በጀት ዓመት የህዝብን መሠረታዊ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው።   በዘንድሮ በጀት ዓመት መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ወደ ተግባር በማሸጋገር ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለህዝብ ተደራሽ ማድረግ መቻሉን ለአብነት አንስተዋል። ይሄን ውጤታማ ስራ በማጠናከርና በማስፋት የላቀ ውጤት ለማስመዝገብ ርብርቡ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። እንደ ከንቲባ ከድር ጁሃር ገለፃ ፤በአስተዳደሩ የገጠሩን ማህበረሰብ ከተረጂነት ወደ አምራችነት ለማሸጋገር እና የከተማውን የኑሮ ውድነትና የስራ አጥነት ጥያቄዎች ለማቃለል የተሰሩ ስራዎች በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ።   በግማሽ በጀት ዓመቱ የነዋሪዎችን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ እየተከናወኑ የሚገኙ 167 ነባርና አዳዲስ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው በጀት፣ ጊዜና ጥራት ተጠናቀው ለህብረተሰቡ አገልግሎት እንዲሰጡ የተቀናጀ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ በበኩላቸው፤ ባለፉት ስድስት ወራት እየተከናወኑ የሚገኙት የኮሪደር ልማት እና የተለያዩ መሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች ድሬዳዋን የምስራቁ የሀገራችን ክፍል ተመራጭ የንግድና የኢንዱስትሪ ማዕከል የማድረጉ ጉዞን እያሳኩ መሆኑን ተናግረዋል።   እየተሰሩ የሚገኙት ልማቶች ድሬዳዋን ፅዱና ውብ የኑሮና የስራ ማዕከል ማድረጋቸውን በመጠቆም እነዚህን ስራዎች በላቀ ቅንጅትና ርብርብ ከዳር የማድረሱ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በግምገማ መድረኩ ላይ የተሳተፉት የድሬደዋ አስተዳደር ከንቲባ የኢኮኖሚ እና የማህበራዊ ዘርፎች አማካሪዎች ፍቃዱ በየነ (ዶ/ር) እና ሰይፉ ታደሰ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በግማሽ በጀት ዓመቱ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ በጤናና በትምህርት ተደራሽነትና ጥራት ላይ የተሰሩ ስራዎች አበረታች መሆናቸውን አንስተዋል። በቀሪው ግማሽ በጀት ዓመት የማዘጋጃ ቤት አገልግሎት ገቢን እና ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የተጀመሩትን ስራዎች በላቀ ጥራትና ውጤት ዳር ማድረስ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባም አንስተዋል። የሴክተር ተቋማት አመራሮች በበኩላቸው፤ በግማሽ በጀት ዓመቱ የተከናወኑት የልማት ስራዎችን በማሳደግ እና ክፍተቶችን በማረም የሚፈለገውን ውጤት ለማምጣት በቁርጠኝነት እንደሚተጉ አረጋግጠዋል።
በክልሉ በጤና ተቋማት ወቅቱን የተከተለ የዲጂታል አሰራርን በመተግበር የእናቶችን ጤና ለመጠበቅ ትኩረት ተደርጓል
Jan 9, 2026 141
ሰመራ፤ ጥር 1/2018(ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል በጤና ተቋማት ወቅቱን የተከተለ የዲጂታል አሰራርን በመተግበር የእናቶችን ጤና ለመጠበቅ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ጤና ቢሮ ገለፀ። ቢሮው "ፈጠራና ዘላቂ ፋይናንስ ለእናቶች ጤና" በሚል መሪ ሐሳብ ከዛሬ ጀምሮ ለቀጣይ አንድ ወር በተለያዩ ኹነቶች የሚከበረውን የእናቶች ጤና ወርን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል። የክልሉ ጤና ቢሮ ምክትል ሃላፊ ዊቲካ ኖሬ በመግለጫቸው እንዳሉት የእናቶችን ጤና መጠበቅ ሲቻል የቤተሰብና የህብረተሰብ ጤና የተጠበቀና ጤናማ ትውልድ ማፍራት ያስችላል። በዚህም በቀጣይ በሚከናወኑ ኹነቶች ፈጠራና ክህሎትን በማሳደግ እንዲሁም በጤና ተቋማት የማዋለጃ ቁሳቁሶችን ማዘመንና ወቅቱን የተከተለ የዲጂታል አሰራር ላይ ትኩረት በማድረግ ስራዎች ይከናወናሉ ብለዋል። ዘላቂነት ያለው የገንዘብ ምንጮችን በማጎልበት በእናቶች ደህንነት እና ጤና ላይ ከአጋር አካላት ጋር በትብብር እንደሚሰራም አስረድተዋል። በተለይም አቅመ ደካማ እናቶችን በኢኮኖሚ ራሳቸውን እንዲችሉ ከባለሃብቶችና ባለድርሻ አካላት ጋር በመስራትና በአካባቢ ያለን ፀጋ በመጠቀም የገንዘብ ማግኛ አማራጮችን የማስፋት ስራም ይሰራል ብለዋል። በዚሁ በእናቶች ወር ከሚከናወኑት የንቅናቄ ስራዎች መካከል በተለይም የአርብቶ አደሩ አካባቢ እናቶች በጤና ተቋማት ብቻ እንዲወልዱና የህክምና ክትትላቸውን እንዲያደርጉ ግንዛቤ የማሳደግ ስራ እንደሚሰራም ገልጸዋል። በተጨማሪም ከተንቀሳቃሽነት የኑሮ ዘይቤ ይልቅ በቋሚ ስፍራ እንዲኖሩ የሚያስችሉ ተግባራትም በትኩረት ይከናወናሉ ብለዋል። በክልሉ የጤና ክትትል የሚደረግላትና ደህንነቷ የተጠበቀ እናት እንድትኖር የሚከናወኑ ተግባራት እንዲጠናከሩ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ሚናቸውን እንዲያጠናክሩ ጠይቀዋል። በቅርቡ የተከፈተው የዱብቲ የእናቶችና ህፃናት ህክምና ማዕከልን እንደ አብነት ያነሱት ምክትል ሃላፊው፤ መሰል የጤና ተቋማትን ማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቶ የሚሰራበት መሆኑን ገልፀዋል። በእናቶች ጤንነትና ደህንነት ላይ የሚሰሩ ስራዎች መመዝገብ፣ መከታተልና ማስቀመጥ ላይ ትኩረት ተደርጎ እንደሚከናወንም ነው ያስረዱት።      
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም