ቀጥታ፡
ማህበራዊ
ህዝቡ ዴሞክራሲያዊ መብቱን በአግባቡ መጠቀም እንዲችል ከጸጥታ አንጻር በቂ ዝግጅት ተድርጓል - የአማራ ክልል ፖሊስ
May 27, 2026 259
ባህር ዳር፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ህዝቡ በጠቅላላ ምርጫው ዴሞክራሲያዊ መብቱን በአግባቡ መጠቀም እንዲችል ከጸጥታ አንጻር በቂ ዝግጅት መደረጉን የክልሉ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ አስታወቀ። የክልሉ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ ኮሚሽነር ጀነራል ዘላለም መንግስቴ (ዶ/ር) ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊነት የተደረጉ ዝግጅቶችን አስመልክተው ዛሬ መግለጫ ሰጥተዋል። ኮሚሽነር ጀነራል ዘላለም መንግስቴ (ዶ/ር) በሰጡት መግለጫ እንዳሉት፤ በክልሉ በተቀናጀ አግባብ በተሰራው የሰላም ማስከበር ስራ ውጤት ተመዝግቧል። በተለይም 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በስኬት እንዲጠናቀቅ የሚያስችሉ፣ ፀጥታን የሚያጠናክሩ ተግባራት ሲከናወኑ መቆየታቸውን ተናግረዋል። የክልሉ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ መብቱን በአግባቡ መጠቀም እንዲችል ከጸጥታ አንጻር በቂ ዝግጅት መደረጉንም አረጋግጠዋል። ህዝቡ ሰላምን የሚያጠናክር እንቅስቃሴን በቁርጠኝነት እያገዘና እየደገፈ እንደሆነም አስረድተዋል። የክልሉ ፖሊስ ከህብረተሰቡና ከሌሎች የፀጥታ መዋቅሮች ጋር በመሆን ምርጫው በስኬት እንዲጠናቀቅ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስታውቀዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በያቤሎ ከተማ የሚገኘውን የቦረና ባሕል ማዕከል መረቁ
May 27, 2026 325
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19 /2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በያቤሎ ከተማ የሚገኘውን የቦረና ባሕል ማዕከል ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምረቃው ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ በቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው በ2013 ዓ.ም የመሰረት ድንጋይ ተቀምጦለት የነበረውና ዛሬ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው የባህል ማዕከል፤ በመደመር መጽሐፍ ሽያጭ የተገነባ መሆኑን ጠቁመዋል። የባሕል ማዕከሉ በ57.6 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ እንደሆነም ገልጸዋል። ማዕከሉ የገዳን ሥርዓት ለማሳየት በልዩ ሁኔታ ዲዛይን የተደረገ ሲሆን በአንድ ጊዜ እስከ 2000 ሰዎች ማስተናገድ አቅም ያለው የስብሰባ አዳራሽ እና የቅርስ ሙዚየምን አካቶ መገንባቱን አመልክተዋል። በተጨማሪም ማዕከሉ የቦረናን ህዝብ ባሕል፣ ታሪክ እና ፍልስፍና ለትውልድ የማሸጋገር ቁልፍ ሚና ይኖረዋልም ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።
የአዲስ አበባ ፖሊስን ተቋማዊ ጥንካሬና ክብር የሚያስጠብቅ ውጤታማ የሪፎርም እርምጃ እየተወሰደ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 27, 2026 278
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ፖሊስን ተቋማዊ ጥንካሬና ክብር የሚያስጠብቅ ውጤታማ የሪፎርም እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ፖሊስ በ100 ቀናት ዕቅድ የተከናወኑ የሪፎርም ሥራዎች አፈፃጸም ማጠቃለያ የግምገማ መድረክ በዓድዋ ድል መታሰቢያ አካሂዷል። በመድረኩ የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል አስራት ዴኔሮ እንዲሁም የጠቅላይ መምሪያው ከፍተኛ አመራሮችና አባላት ተገኝተዋል። ከንቲባ አዳነች በዚሁ ጊዜ፤ በሀገራዊ ለውጡ ማግስት በፀጥታና ደኅንነት ተቋማት ተልዕኮን በብቃት መወጣት የሚያስችል ውጤታማ የሪፎርም እርምጃ መወሰዱን አስታውሰዋል።   በፀጥታና ደኅንነት ተቋማት ከተወሰደው ውጤታማ የለውጥ እርምጃ አንፃርም የአዲስ አበባ ፖሊስ ተልዕኮን በብቃት መወጣት የሚያስችል ሪፎርም እንደሚያስፈልገው ተናግረዋል። በዚህም የአዲስ አበባ ፖሊስን ተቋማዊ ጥንካሬና ክብር የሚያስጠብቅ ውጤታማ የሪፎርም እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን አንስተዋል። በተቋሙ የሪፎርም እርምጃ የሚደረገው ድጋፍና ክትትልም የሠራዊቱን ሎጀስቲክስ፣ ሞራልና ሙያዊ ሥነ-ምግባር በመገንባት ተልዕኮን በብቃት መወጣት የሚያስችል እንደሆነ አስረድተዋል። የአዲስ አበባ ፖሊስ 3ኛዋን ዓለምአቀፍ የዲፕሎማሲ ማዕከል ከተማ ሰላምና ደኅንነትን በማስጠበቅ በወንጀል መከላከልና የሕግ የበላይነትን በማስፈን የተጣለበትን ከፍተኛ ኃላፊነት እየተወጣ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የፖሊስ ሠራዊትን የመኖሪያ ቤት ፍላጎት ለመፍታት የመጀመሪያው ምዕራፍ የመኖሪያ መንደር ግንባታ በመጪው ሰኔ ወር እንደሚጀመር አስታውቀዋል። በቀጣይም ፖሊስ በመዲናዋ ለሚከናወኑ ሁለንተናዊ የልማት ሥራዎች የሚያበረክተውን ጉልህ አስተዋጽኦ የበለጠ በማላቅ ከከተማዋ ፈጣን ዕድገት ጋር አብሮ መጓዝ እንደሚገባው አስገንዝበዋል። የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ዋና አዛዥ ሌተናል ጀነራል አስራት ዴኔሮ በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ ፖሊስ 118 ዓመታትን ያስቆጠረ ታሪክ ያለው አንጋፋ ተቋም መሆኑን አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅትም የመዲናዋን ሰላምና ደኅንነት 24/7 በማስጠበቅ ግዳጁን በብቃት እየተወጣ መሆኑንም ተናግረዋል። የተቋሙ ሁለንተናዊ የሪፎርም እርምጃ ተቋማዊ ተልዕኮን በብቃት በመወጣት የሠራዊት አባላቱን ጥቅምና ክብር የሚያስጠብቅ መሆኑን ገልጸዋል።
የአፍሪካ ዲፕሎማሲ ማዕከል የሆነችውን አዲስ አበባን የሚመጥን የፖሊስ ሠራዊት ለመገንባት ውጤታማ ስራ እየተሰራ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 27, 2026 194
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ዲፕሎማሲ ማዕከል የሆነችውን አዲስ አበባን የሚመጥን የፖሊስ ሠራዊት ለመገንባት ውጤታማ ስራ እየተሰራ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በመልዕክታቸው፤ በየደረጃው የሚገኙ የአዲስ አበባ ከተማ የፖሊስ አመራሮች እና አባላት ባለፉት 100 ቀናት በዕቅድ የተከናወኑ የሪፎርም ሥራዎችን ማጠቃለያ ግምገማ ዛሬ ማካሄዳቸውን ጠቁመዋል። በዚህ የግምገማ መድረክ ላይ የተገኙት ከንቲባዋ፤ ሠራዊቱ እያከናወናቸው ለሚገኙ ውጤታማ ተግባራት አድናቆታቸውን በመግለጽ አበረታተዋል። ባለፉት 100 ቀናት በመልካም አስተዳደርና አገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ በተያዙ የሪፎርም ዕቅዶች ላይ ያተኮሩ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውንም ገልጸዋል።   ይህም እየተከናወነ ያለው የሪፎርም ሥራ፣ እያደገችና እየዘመነች ከመጣችው የአፍሪካ እና ሶስተኛዋ የዓለም የዲፕሎማሲ ማዕከል የሆነችውን አዲስ አበባ የሚመጥን የፖሊስ ሠራዊት መገንባትን ያለመ መሆኑን ነው ያመለከቱት። ተቋሙ ገለልተኛ ሆኖ በሕግና በሕዝብ የተጣለበትን አደራ በአግባቡ የሚወጣ፣ በሥነ-ምግባር ክብሩ የተጠበቀ፣ በሰው ኃይል አቋሙ ብቁ እንዲሁም በአሠራሩ ከዘመኑ ጋር የሚራመድ እንዲሆን ለማስቻል በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝም ተናግረዋል። የከተማ አስተዳደሩና ሕዝቡ፣ አንዳንዶች የሚፈጽሙትን የተቋሙንና የሠራዊቱን ስም የሚያጠለሹ ስህተቶች እያረሙ፣ በጥሩ ሁኔታ የሚሠሩትን ደግሞ እያበረታቱ፣ ለሚከናወኑ መልካም ሥራዎች ሁሉ ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
የአካል ጉዳተኞች ማኅበራዊ አካታችነት ለሁለንተናዊ እድገት
May 27, 2026 109
  በኢትዮጵያ የአካል ጉዳተኞችን ማኅበራዊ አካታችነት ማረጋገጥ ለሀገር ግንባታ፣ ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት መስፈንና ለዘላቂ ሰላም መሠረት መሆኑ ይታመናል። በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ ከ20 ሚሊዮን በላይ አካል ጉዳተኞች እንደሚኖሩ የሚገመት ሲሆን፣ ይህን ያህል የኅብረተሰብ ክፍል ያገለለ የልማት ጉዞ ሰብአዊ ዕሴቱ የጎደለና ፍትሐዊነት የራቀው ነው። በመሆኑም መንግሥት አካል ጉዳተኝነትን ዝቅ አድርጎ የመመልከት የተሳሳተ አመለካከትን በመቀየር፣ እነዚህ ዜጎች በሁሉም የሥራ ዘርፎች የላቀ ውጤት ማሳየት የሚችሉ የሀገር ባለቤትና ገንቢዎች መሆናቸውን በመገንዘብ የአካታችነት መርህን እየተገበረ ይገኛል። ማንኛውንም በአካል ጉዳተኝነት ላይ የተመሠረተ አድልዎ መከላከልና እኩል የሕግ ጥበቃ እንዲያገኙ ማድረግ የመንግሥት ዋነኛ አቋም ነው። ባለፉት ዓመታት የአካል ጉዳተኞችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ስፋት ያላቸው ተግባራት ተከናውነዋል። በተለይም ዜጎች በማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ እኩል ተሳታፊ እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታዎችን የመፍጠር ሥራ ትኩረት ተሰጥቶታል። የአካል ጉዳተኞችን የእንቅስቃሴ ችግር ለመቅረፍ እንዲቻል የሰው ሠራሽ አካልና የአካል ድጋፍ ማምረቻ ማዕከላትን የማዘመን ሥራ ተሠርቷል። ለዚህም በዘርፉ የተሃድሶ የልህቀት ማዕከል ተገንብቶ አገልግሎት እንዲጀምር የተደረገ ሲሆን፣ ከ5 ሺህ በላይ አካል ጉዳተኞች ከቀረጥና ታክስ ነፃ የሆኑ ተሸከርካሪዎችን ከውጭ በማስገባት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ተደርጓል። ይህ አገልግሎት በማዕከል ብቻ ሳይወሰን በክልሎች ጭምር ተደራሽ እንዲሆን በማድረግ በክልሎች ለሚገኙ በመቶዎች የሚቆጠሩ ዜጎች የአካላዊ ተሃድሶ ድጋፍ ተሰጥቷል። የአገልግሎት አሰጣጡን ይበልጥ ቀልጣፋ ለማድረግም ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የዲጂታል (ኢ-ሰርቪስ) አሠራር ተግባራዊ ሆኗል። ይህም አካል ጉዳተኞች የሚፈልጉትን መረጃና አገልግሎት በፍጥነት እንዲያገኙ አስችሏል። ከዚህ በተጨማሪ አካል ጉዳተኞች በማኅበር ተደራጅተው መብቶቻቸውን እንዲያስከብሩና በፈጠራ ሥራዎች እንዲሰማሩ የቴክኒክና የፋይናንስ ድጋፎች ሲደረጉ ቆይተዋል። መንግሥት የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል በሚያደርገው ጥረት የአካል ጉዳተኞችንና አቅመ ደካማ ወገኖችን ቤት በማደስ እንዲሁም በከተሞች የምገባ ማዕከላትን በማስፋፋት "ማንንም ወደኋላ እንዳይቀር" የሚለውን መርሕ በተግባር ሲያሳይ ቆይቷል። መንግሥት የአካል ጉዳተኞችን መብት ይበልጥ የሚያስከብሩ የሕግና የፖሊሲ ማሻሻያዎችን በማድረግ ለመስራት አቅዷል ። አካል ጉዳተኞች ከድህነት እንዲወጡና የትምህርት ሽፋናቸው እንዲያድግ ልዩ ትኩረት መስጠት ያስፈልጋል ። በተለይም በሥራ ስምሪት ረገድ ያላቸውን መብት በማረጋገጥ፣ በፖሊሲ ቀረጻና በስትራቴጂ አተገባበር ላይ ንቁ ተሳታፊ እንዲሆኑ ማድረግ ይገባል ። የማኅበረሰቡን ግንዛቤ በማሳደግ ስለ አካል ጉዳተኝነት የሚታየው አዎንታዊ አመለካከት እንዲጠናከርና ፍትሕ የሰፈነበት አካታች ማኅበረሰብ እንዲገነባ በትጋት ይሠራል። መንግሥት የጀመራቸውን ግዙፍና አካታች ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት በማጠናቀቅ፣ የአካል ጉዳተኞችን ደህንነት፣ ጤንነትና ውጤታማነት የሚያረጋግጥ የብልፅግና ጉዞን በጋራ ማሳካት አስፈላጊ ነው።
የአረፋ በዓል የመተሳሰብ፣ የፍቅርና የአንድነት መገለጫ ነው
May 27, 2026 105
ወላይታ ሶዶ/ዲላ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል የመተሳሰብ፣ የፍቅርና የአንድነት መገለጫ መሆኑ ተመለከተ። 1ሺህ 447ኛ የኢል አል አድሃ (አረፋ) በዓል በወላይታ ሶዶ እና በዲላ ከተሞች በሃይማኖታዊ ሥርዓቶች ተከብሯል።   በወላይታ ሶዶ ከተማ የሐምዛ መስጂድ ዋና ኢማም ኡስታዝ ሼህ አሊ ሀምዛ ለኢዜአ እንደገለጹት የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል የመተሳሰብ፣ የፍቅርና የአንድነት መገለጫ ነው። ምዕመናን ፍቅርና አንድነትን በማጠናከር ኃይማኖታዊ ትዕዛዙን በመፈጸም የሚያከብሩት መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም በቤተሰባዊነት፣ በይቅርታና ሰላምን በሚያጠናክሩ ተግባራት የሚከበር መሆኑን ጠቁመው ሙስሊሙ ህብረተሰብም ይህንኑ ሊፈጽም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።   የወላይታ ዞን ከፍተኛ ሸሪአ ፍርድ ቤት ቃዲ ሼህ ጁዋር ሀሚድ በበኩላቸው ኢድ አል አድሃ በዓል በሀይማኖቱ ተከታዮች ዘንድ አንድነትን ይበልጥ በማጠናከር የተቸገሩትን በመርዳትና ከጎረቤቶች ጋር በደስታ የሚከበር መሆኑን ተናግረዋል።   በዓሉ መልካም ተግባራትን በማከናወንና እርስ በርስ በመደጋገፍ እንዲሁም ያለውን በመካፈል የሚከበር መሆኑን የጠቀሱት ደግሞ አቶ አኑዋር አበራ እና ጃፍር አብድሽኩር ናቸው።   በተያያዘም በዲላ ከተማ የቢላል መስጅድ ኢማም ኡስታዝ ሸህ ሱፍያን ጀማል አረፋ የመረዳዳት እሴት የሚጎላበት በዓል መሆኑን ጠቅሰዋል።   የኢድ አል አደሃ (አረፋ) በአል ያለንን ተካፍለን ማሳለፍን የምንማርበት ነው ያሉት ደግሞ የዲላ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ሰብሳቢ ኡስታዝ አብዱረህማን አብዱቄ ናቸው።   በአሉ ሲከበር ይህንን መንፈሳዊ እሴት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ አመልክተዋል።
በአረፋ በዓል ጎልቶ የሚታየውን የአብሮነትና የመደጋገፍ እሴት አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል
May 27, 2026 139
ወልቂጤ/ሆሳዕና፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ በአረፋ በዓል ጎልቶ የሚታየውን የአብሮነትና የመደጋገፍ እሴት አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ገለጸ። 1ሺህ 447ኛው የኢድ አል አድሀ (አረፋ) በዓል በወልቂጤ እና በሆሳዕና ከተሞች በድምቀት ተከብሯል። በከተሞቹ ያሉ የሃይማኖቱ ተከታዮች የመታዘዝና የመተዛዘን ተምሳሌት የሆነውን የአረፋ በዓል የሌላቸውን ወገኖች በማገዝ በደስታ እያከበሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ኡስታዝ በህጃ አብዱልጀሊል በእዚህ ወቅት እንዳሉት፣ የአረፋ በዓል የአብሮነት እሴቶች የሚጎሉበት በመሆኑ በእምነቱ ተከታዮች ዘንድ ትልቅ ቦታ አለው። የሌላቸውን ወገኖች በማሰብ በዓሉን በጋራ በደስታ ማክበር ከእምነቱ ተከታዮች እንደሚጠበቅ ገልጸው፤ በዓሉ ያለውን የሰላም፣ የፍቅርና የመተሳሰብ እሴት በማጎልበትና መልካም ተግባር በመፈጸም ማሳለፍ እደሚገባ አስገንዝበዋል።   የዒድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል የእርስ በእርስ መደጋገፍ የሚጎላበትና ሰላም የሚሰበክበት ታላቅ በዓል ነው ያሉት ደግሞ የወልቂጤ ከተማ ከንቲባ ሙራድ ያሲን ናቸው። የበዓሉ የአብሮነት እሴቶች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የከተማው አስተዳደር የበኩሉን እየተወጣ መሆኑንም ተናግረዋል።   ከበዓሉ ተዳሚዎች መካከል ሲራጅ ኑራን እንዳሉት፣ አረፋ እርድ የሚከወንበት በዓል በመሆኑ ያለው ከሌለው ጋር ተካፍሎ የሚበላበት፣ መተዛዘንና አብሮነት ጎልቶ የሚታይበት ነው።   በዓሉን ስናከብር ፈጣሪ የሚወደውን በጎ ተግባር በመፈጸም፣ የተቸገሩና አቅመ ደካሞችን በማሰብ መሆን እንዳለበት የተናገሩት ደግሞ አብዱራህማን ጀማል የተባሉ ታዳሚ ናቸው። በተመሳሳይ የአረፋ በዓል በሆሳዕና ከተማ አብዮ ኤርሳሞ መታሰቢያ ስታዲየም በተለያዩ ሀይማኖታዊ ሥርዓቶች ተከብሯል።   በበዓሉ ላይ የሀድያ ዞን እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሰብሳቢ ኡስታዝ ሱልጣን ኡስማን እንደገለጹት፣ የአረፋ በዓል የመስዋዕትነት፣ የእዝነትና የርህራሄ በዓል ነው። በመሆኑም ህዝበ ሙስሊሙ በዓሉን በአቅራቢያው ያሉ አቅመ ደካሞችን በመርዳትና አብሮነቱን በሚያጠናክር መልኩ ማክበር እንዳለበት አስገንዝበዋል።   ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል ወጣት ነጃት አበበ በሰጠችው አስተያየት የመታዘዝና የመተዛዘን ተምሳሌት የሆነውን የኢድ አል አደሃ በዓልን የሌላቸውን ወገኖች በመጠየቅና በማገዝ በደስታ እያሳለፈች መሆኗን ተናግራለች። የሀይማኖቱ አስተምህሮ በሚያዘው መሰረት አቅመ ደካማ ወገኖችን በመደገፍ እያሳለፉ መሆናቸውን የተናገሩት ሌላኛው የከተማ ነዋሪ ደግሞ አቶ አብድልፈታ ቢላል ናቸው፡፡
የአረፋ በዓልን በአብሮነት እና የተቸገሩ ወገኖችን በመደገፍ እያከበርን ነው
May 27, 2026 167
አዳማ/አምቦ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ )፡-የኢድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓልን በአብሮነት እና የተቸገሩ ወገኖችን በመደገፍ እያከበርን ነው ሲሉ የአዳማ እና የአምቦ የእምነቱ ተከታዮች ተናገሩ። 1447ኛው የኢድ አል-አድሃ አረፋ በዓል በአዳማ ከተማ የኢድ አደባባይ በተለያዩ ሃይማኖታዊ ክዋኔዎች በድምቀት ተከብሯል። የአዳማ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሰብሳቢ ሼህ ሙሐመድሁሴን አህመድ እንደገለፁት የኢድ አል-አድሃ በዓል በሕዝበ ሙስሊሙ ዘንድ በታላቅ ድምቀት የሚከበር ነው። ሕዝበ ሙስሊሙ በዓሉን በሰላም፣ በፍቅርና አብሮነት ማሳለፍ እንዳለበት ተናግረው እርድ ሲከናወን አቅም ለሌላቸው በማካፈል ማክበር እንደሚገባው አስገንዝበዋል። ሕዝበ ሙስሊሙ የአካባቢውንና የሀገራቸውን ሰላም በአንድነት እንዲጠብቅ ከሀገር ሽማግሌዎችና ከሌሎች የሃይማኖት አባቶች ጋር በትብብር እየሰራን እንገኛለን ነው ያሉት።   በአዳማ በተከበረው በዓል ላይ የተገኙት ሼህ ሸሪፍ ኢብራሂም በበኩላቸው የአረፋ በዓል በእስልምና ትልቅ ቦታ ያለው ታላቅ የአደባባይ በዓል መሆኑን ገልጸዋል። በበዓሉ ያለው የሌለውን እንዲያስታውስ ምስኪኖችና ድሆችን በማብላት ማሳለፍ አለበት ያሉት ሼህ ሸሪፍ ለቤታቸው ከሚያርዱት በማካፈል ከሌላቸው ድሆች ጋር አብረን የምናሳልፈው በዓል ነው ብለዋል። የአረፋ በዓል በሺህዎች የሚቆጠሩ ሙስሊሞች በአደባባይ ወጥተው በአንድነት የሚያከብሩት ታላቅ በዓል መሆኑን የገለፁት ደግሞ ሼህ ሱልጣን ቃሲም ናቸው። በተክቢራና በሃይማኖታዊ ክንውኖች በመመራት በአደባባይ ወጥተን የምንሰግድበትና ፈጣሪያችንን የምናስታውስበትና የምናመሰግንበት በዓል ነው ብለዋል። እርድ የሚፈጽሙ አካላት ለሌላቸው በማካፈል በዓሉን በጋራ አብሮ ማሳለፍ አለባቸው ያሉት ሼህ ሱልጣን በመረዳዳትና በመተጋገዝ በአንድነትና በርህራሄ በዓሉን ማክበር አለብን ነው ያሉት።   በተመሳሳይ በአምቦ ከተማ የእስልምና እምነት ተከታዮች የአረፋ በዓልን የተቸገሩ ወገኖችን በመደገፍ እያከበሩ መሆኑን ገልጸዋል። የበዓሉ ታዳሚዎች በዓሉን ሲያከብሩ የተቸገሩ ወገኖችን በመርዳትና ማዕድ በማጋራት መሆኑን ተናግረዋል። የአምቦ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሰብሳቢ ኡስታዝ አህመድ ስራጅ፣ የዘንድሮውን በዓል ልዩ የሚያደርገው በተለያዩ ምክንያቶች ችግር ላይ የሚገኙ ወገኖችን በመደገፍና ማዕድ በማጋራት መከበሩ እንደሆነ ገልጸዋል።   የአምቦ ከተማ ከንቲባ አቶ ሃጫሉ ገመቹ በበዓሉ ላይ ባስተላለፉት መልእክት፤ የከተማው ሕዝበ ሙስሊም በዓሉን ለከተማዋ ዕድገት በጋራ በመትጋት ሊያከብረው ይገባል ብለዋል። ሕዝበ ሙስሊሙ የተገነቡ የልማት መሠረተ ልማቶችን በመንከባከብና ወደፊት ለሚከናወኑ ሥራዎችም የተለመደ ትብብሩን እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።   ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል ወይዘሮ አሚና ሹና የኢድ አል-አድሃ በዓል ሲከበር ቅራኔዎችን በማስወገድ፣ በአብሮነት፣ በመተጋገዝና በመረዳዳት መሆን እንዳለበት ገልጸዋል። ወጣት ሰፊዲን ሙሀመድ በዓሉን የእምነቱ አስተምህሮ በሚያዘው መሠረት ከቤተሰቦቹና ከጓደኞቹ ጋር በደስታ እያከበረ መሆኑን ተናግሯል።  
የኢድ አል አድሃ አረፋ በዓል ያለንን በጎ የመረዳዳትና የአብሮነት እሴት የምናጠናክርበት በዓል ነው
May 27, 2026 112
ቦንጋ ፤ ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፦ የኢድ አል አድሃ አረፋ በዓል ያለንን በጎ የመረዳዳትና የአብሮነት እሴት የምናጠናክርበት በዓል ነው ሲሉ የቦንጋ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሰብሳቢ ኡስታዝ አይደር ሁሴን ተናገሩ። 1447ኛው የዒድ አል-አድሐ (አረፋ) በዓል በተለያዩ ዝግጅቶች በቦንጋ ከተማ በድምቀት ተከብሯል ። የአረፋ በዓል በእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ከሚከበሩ ታላላቅ በዓላት መካከል አንዱ ሲሆን የታዛዥነት፣ የመስዋዕትነት መገለጫ ሲሆን የመተሳሰብ፣ የመረዳዳት፣ የሰላምና የአብሮነት እሴቶች ይበልጥ የሚጎላበት ነው።   የቦንጋ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሰብሳቢ ኡስታዝ አይደር ሁሴን በወቅቱ እንደገለፁት፤ የአረፋ በዓል ለአላህ ያለንን ፍፁም ታዛዥነት የምናድስበት በዓል ነው። በተጨማሪም የኢድ አል አድሃ አረፋ በዓል ያለንን በጎ የመረዳዳትና የአብሮነት እሴት የምናጠናክርበት በዓል ነው ብለዋል። ህዝበ ሙስሊሙ ለሀገርና ለአካባቢው ሰላምና ልማት ያለው አስተዋፅኦና ተሳትፎውን የሚያጠናክርበት መሆኑን ጠቅሰው፣ ወጣቶችም ከዚህ በዓል መልካም አርዓያነትን ሊማሩ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። በበዓሉ ላይ ተገኝተዉ መልዕክት ያስተላለፉት የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ፣ በለውጡ መንግስት ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት በሚያደርገው ጥረት የሙስሊሙ ማህበረሰብ ድርሻ የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።   የሙስሊሙ ማህበረሰብ ለሀገርና ለዞኑ ሰላምና ልማት እያበረከተ ያለው አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰው የእምነቱ ተከታዮች በዓሉን በሀይማኖቱ አስተምህሮ መሰረት በመረዳዳትና በመተሳሳብ እንዲያከብሩም አሳስበዋል። የካፋ ዞን እስልምና ከፍተኛ ምክር ቤት ሰብሳቢ ኡስታዝ መሐመድ ጅብሪል የአረፋ በዓል በተለያዩ ሀይማኖታዊ ስርዓቶች የሚከበር የታዛዥነትና የመስዋዕትነት በዓል ነው ብለዋል። ህዝበ ሙስሊሙ በዓሉን የተቸገሩትን በመርዳት፣ የደከሙትን በማበርታት በአብሮነትና በፍቅር ሊያከብረው እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ከእምነቱ ተከታዮች መካከል አቶ አንዋር ሀሰንና አቶ ከድር ሁሴን በዓሉን የተቸገሩትን በመርዳትና እርስ በእርስ በመደጋገፍ ለማክበር መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ከበዓሉ አስተምህሮ ታዛዥነትንና የመልካምነት እሴትን በመላበስ በአንድነትና በአብሮነት በዓሉን ማክበር እንደሚገባ አንስተው በዓሉ የሰላም፣ የደስታና የጤና እንዲሆንም ተመኝተዋል።  
ህዝበ ሙስሊሙ የአረፋን በዓል ሲያከብር ለሌላቸው ወገኖች በማካፈል ሊሆን ይገባል
May 27, 2026 118
ጋምቤላ፤ ግንቦት 19/ 2018 (ኢዜአ) ፡-ህዝበ ሙስሊሙ የአረፋን በዓል ሲያከብር ለሌላቸው ወገኖች በማካፈል ሊሆን እንደሚገባ የጋምቤላ ክልል እስልምና ከፍተኛ ምክር ቤት አስገነዘበ። 1 ሺህ 447ኛው የኢድ ዓል አድሃ (አረፋ) በዓል በጋምቤላ ከተማና አካባቢው በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስነ-ስርዓቶች በድምቀት ተከብሯል። የክልሉ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዚዳንትኡስታዝ ሁሴን ካዩራ ባስተላለፉት መልዕክት ህዝበ ሙስሊሙ የአረፋ በዓልን ሲያከብር በመተዛዘን፣ በመደጋገፍና የተቸገሩ ወገኖችን በማገዝ ሊሆን ይገባል ብለዋል።   በመሆኑም ህዝበ ሙስሊሙ የአረፋን በዓል ሲያከብር ቤት ካፈራው አንድ ሶስተኛውን ለሌላቸው ወገኖች በማካፈል ሊሆን ይገባል ብለዋል። የኢድ አል አድሀ አረፋ በዓል በእስልምና እምነት አስተምህሮ የታዛዥነትና የጽናት ተምሳሌት መሆኑን ጠቁመው ምዕመኑ እንደ እምነቱ አስተምህሮ በዓሉን ሊያከብር እንደሚገባ ገልጸዋል። ህዝበ ሙስሊሙ አብሮነቱንና አንድነቱን በማጠናከር ለክልሉ ዘላቂ ሰላምና ልማት መረጋገጥ የበኩሉን ሚና ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል። በተጨማሪም ዘንድሮ የሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ እንዲሆን ህዝበ ሙስሊሙ የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባም ፕሬዚዳንቱ አስገንዝበዋል።   ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል ሀጅ ሀሰን ሙሀመድ በሰጡት አስተያየት የአረፋ በዓል በአንድነትና በአብሮነት የሚከበር ታላቅ በዓል ነው ብለዋል። ይህንንም ታሳቢ በማድረግ ቤት ካላቸው ላይ ለሌላቸው በማካፋል በዓሉን በአንድነትና በፍቅር እያከበሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የአረፋ በዓል ህዝበ ሙስሊሙ ፍቅርንና አንድነትን አጉልቶ የሚያሳይበት በዓል መሆኑን የገለጹት ደግሞ ሌላው የበዓሉ ታዳሚ ኡስታዝ ሼህ በድሩ ጅማ ናቸው። በመሆኑም በዓሉን አቅመ ደካሞችንና ረዳት የሌላቸውን ወገኖች በመጠየቅና በመደገፍ እያከበሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።    
ህዝበ ሙስሊሙ የእስልምና እምነት ትእዛዝ የሆነውን የተቸገሩ ወገኖችን በመደገፍ በዓሉን ሊያከብር ይገባል
May 27, 2026 141
ጅግጅጋ፣ ግንቦት 19 / 2018 (ኢዜአ)፡- ህዝበ ሙስሊሙ የእስልምና እምነት ትእዛዝ የሆነውን የተቸገሩ ወገኖችን በመደገፍ በዓሉን ሊያከብር ይገባል ሲሉ የሶማሌ ክልል እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሼክ አህመድ መሀመድ ገለጹ። የ1447ኛው የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል በሶማሌ ክልል መዲና ጅግጅጋ ከተማ በታላቅ ድምቀት ተከብሯል። በጅግጅጋ ስታዲየም በተካሄደው የሶላት ስነ-ስርዓት ላይ በርካታ የከተማዋና የአካባቢው የእምነቱ ተከታዮች እንዲሁም የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዓሉን አስመልክቶ የሶማሌ ክልል እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሼክ አህመድ መሀመድ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ህዝበ ሙስሊሙ የእስልምና እምነት ትእዛዝ የሆነውን የተቸገሩ ወገኖችን የመደገፍ ተግባር ሊያጠናክር እንደሚገባ አሳስበዋል። የኢድ አል አድሃ በዓል ዋና መገለጫ መረዳዳትና ማካፈል መሆኑን ገልጸው፣ ሃይማኖታዊ እሴቶችን ጠብቆ ማክበርና እርስ በርስ የመደጋገፍ ተግባራትን ይበልጥ ማጠናከር የእምነቱ ትእዛዝ መፈጸም መሆኑን አስገንዝበዋል። በበዓሉ ስነ-ስርዓት ላይ የተገኙት የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ሙስጠፌ ሙሁመድ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።   ህዝበ ሙስሊሙ በበዓል ወቅትም ሆነ ከበዓል ውጪ ባሉ ቀናት ሁሉ የተቸገሩ ወገኖችን የመደገፍና የመረዳዳት በጎ ባህሉን አጠናክሮ ሊቀጥልበት እንደሚገባ ተናግረዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ አክለውም፥ የክልሉን ሰላምና ልማት በዘላቂነት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ላይ ህዝበ ሙስሊሙ እያደረገ ያለውን ተሳትፎ ይበልጥ እንዲያጠናክር ጥሪ አቅርበዋል። በጅግጅጋ ስታዲየም በታላቅ ድምቀት የተካሄደው የ1447ኛው የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል የሶላት ስነ-ስርዓት በሰላም መጠናቀቁ ታውቋል።  
በዓሉ የተቸገሩትን የምንረዳበት፣አንድነታችንና አብሮነታችንን የምናጠናክርበት ነው-በሐረር የእምነቱ ተከታዮች
May 27, 2026 75
ሐረር፣ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፦የኢድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል የተቸገሩትን የምንረዳበት፣ አንድነታችንና አብሮነታችንን የምናጠናክርበት ነው ሲሉ በሐረሪ ክልል የሚገኙ የእምነቱ ተከታዮች ተናገሩ። በሐረሪ ክልል የኢድ አል-አድሃ አረፋ በዓል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪን ጨምሮ ከፍተኛ አመራሮች እና የእምነቱ ተከታዮች በተገኙበት በሐረር ኢማም አህመድ ስታዲዮም በታላቅ የሶላት ሥነ-ሥርዓት በድምቀት ተከብሯል። በዓሉን እርስ በእርስ በመደጋገፍ፣ ቤት ያፈራውን ለተቸገሩ ወገኖች በማጋራት እናከብራለን ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው ምዕመናን አመልክተዋል። በሶላት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኘችው ማወርዲ ሙህየዲን እንደተናገረችው፤ በዓሉን በመደጋገፍና በአብሮነት እናከብረዋለን ብላለች። በተለይ በጎረቤትና በአካባቢው የሚገኙ የተቸገሩ ወገኖችን በመጠየቅና በማስደሰት በዓሉን በጋራ እንደሚያሳልፉት ገልጻለች። የእስልምና አስተምህሮ በሚያዘው መሠረት የኢድ አል-አድሃ አረፋ በዓልን በመረዳዳትና በመተጋገዝ እናከብራለን ያለው ደግሞ አብዱላዚዝ አብዲ ነው። እንደ ወጣት አብዱላዚዝ ገለጻ፤ እሱና ጓደኞቹ በአካባቢው የሚገኙ ወላጅ አልባ ሕፃናት፣ አቅመ ደካማ አረጋውያንና ሌሎችንም ወገኖች በማብላትና በመደገፍ በዓሉን ለማሳለፍ ተዘጋጅተዋል። ሌላው የእምነቱ ተከታይ ሙስተርያ አደም በበኩሉ፤ በዓሉ ሁሉም በጋራ ተደስተው የሚያሳልፉበት በመሆኑ ከቤተሰብና ከጎረቤቶቻቸው ጋር በአንድነት በደስታ እንደሚያሳልፉት ገልጿል። የኢድ አል-አድሃ አረፋ በዓል በማካፈልና በመደገፍ፣ አብሮነትን በማጠናከር የሚከበር በዓል ነው ያለው ደግሞ ወጣት ሁሴን አብዲ ነው፤ በዓሉንም የተራቡትን በማብላት፣ የታረዙትን በማልበስና በመረዳዳት እንደሚያሳልፈው ተናግሯል።  
የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓልን መተሳሰብ እና አብሮነትን ይበልጥ በሚያጠናክር መልኩ ማክበር ይገባል
May 27, 2026 74
ባህርዳር ፤ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፡- የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓልን መተሳሰብ እና አብሮነትን ይበልጥ በሚያጠናክር መልኩ ማክበር እንደሚገባ የባህርዳር ከተማ አስተዳደር እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ሰብሳቢ ገለጹ። 1447ኛው የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል በባህርዳር ከተማ ጋጃ መስክ የእምነቱ ተከታዮች በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል።   የባህርዳር ከተማ አስተዳደር እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ሰብሳቢ ሼህ መሃመድ ሰኢድ ባስተላለፉት መልዕክት የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓልን ህዝበ ሙስሊሙ ሲያከብር እምነቱ በሚያዘው መሠረት ከሚፈጸመው እርድ አንድ ሦስተኛውን ለምስኪኖችና ለተቸገሩ ወገኖች በማካፈል ሊሆን ይገባል ብለዋል። እንዲሁም በዓሉ ሰላምን የምናጸናበት፣ አንድነትና አብሮነትን ይበልጥ የምናጠናክርበት እንዲሆን ለእምነቱ ተከታዮች መልዕክት አስተላለፈዋል።   በበዓሉ ላይ የተገኙት የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው ህዝበ ሙስሊሙ ሰላምን በመጠበቅ ልማቱ እንዲፋጠን እያደረገ ላለው እገዛ አመስግነዋል። ህዝበ ሙስሊሙ በዓሉን ሲያከብርም አብሮነትና አንድነቱ ይበልጥ በማጠናከር የጀመርነውን ሰላምን አጽንቶና ልማትን አጠናክሮ የማስቀጠል ጉዞውን ይበልጥ ሊያጠናክር እንደሚገባ በማስገንዘብ ነው። በቀጣይ አምስት ዓመትም እጅ ለእጅ ተያይዘን ከተማዋን ኢንቨስትመንትና የቱሪዝም መዳረሻ ከተማ ለማድረግ የጀመርነውን ሥራ አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። የከተማ አስተዳደሩም ህዝበ ሙስሊሙ እንዲፈቱለት በየጊዜው ለሚያነሳቸው ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት የጀመረውን ሥራ ይበልጥ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል።   የበዓሉ ታዳሚ ሼህ አደም ኢሳ እንዳሉት በዓሉን የምናከብረው እምነቱ በሚያዝዘው መሠረት የተቸገሩ፣ ጧሪና ደጋፊ የሌላቸውን አቅመ ደካሞችን በመርዳትና በማገዝ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም በዕለቱ ከምናከናውነው እርድ እምነቱ በሚያዝዘው መሠረት ለተቸገሩ ወገኖች በማካፈል ተደስተው እንዲውሉ በማድረግ ነው።   በዓልን የምናከብረው ካለን ላይ ለተቸገሩ ወገኖች ከማካፈል ባለፈ ሰላምን፣ አንድነትና አብሮነትን በማጠናከር ነው ያሉት ደግሞ መምህር ከድር መሃመድ ናቸው። እንዲሁም በዓሉን ከቤተሰቦቻቸውና ከጎረቤቶቻቸው ጋር በሰላምና በደስታ ለማሳለፍ እንደተዘጋጁም ገልጸዋል።  
የዒድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል ሲከበር ሰላምን በማፅናትና አንድነትን በማጠናከር ሊሆን ይገባል
May 27, 2026 85
ገንዳውሃ/ጎንደር/ ደብረ ብርሃን ፤ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ):- የዒድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል ሲከበር ሰላምን በማፅናትና አንድነትን በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ተመላከተ። የኢድ አል አድሀ አረፋ በዓል ሲከበር ሰላምን በማፅናትና አንድነትን በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ ኢዜአ በገንዳ ውሃ፣ በጎንደርና ደብረ ብርሃን ከተሞች ያነጋገራቸው የእምነቱ ተከታዮች አመልክተዋል። ​የገንዳውኃ ከተማ እስልምና የምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሙሀመድ ኑርዬ እንደገለጹት፣ የአረፋ በዓል የታላቁ ነቢይ ኢብራሂም የታዛዥነትና የመስዋዕትነት ታሪክ የሚዘከርበት ነው። በዚህም የእስልምና እምነት ተከታዮች ሃይማኖታዊ ስርአቱ በሚያዘው መሰረት እርስ በርስ የሚተሳሰቡበትና የአብሮነት እሴት የሚያጎለብቱበት መሆን እንደሚገባው ገልጸዋል። ​ሌላኛው የሀይማኖቱ ተከታይ ሼህ ሙሀመድ ታደሰ በበኩላቸው፣ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በአካባቢው የሚገኙ አቅመ ደካማ ወገኖችን ለመደገፍ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ​የገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ አብዱልከሪም ሙሀመድ በበኩላቸው ህዝበ ሙስሊሙ በዓሉን ሲያከብር የሚያሳየውን መደጋገፍና ወንድማማችነት በሌሎች ጊዜያትም አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስገንዝበዋል።   በተመሳሳይ የኢድ አል አደሃ /አረፋ/ በዓል በጎንደር ከተማ በፋሲለደስ ስታዲዮም በታላቅ ሃይማኖታዊ ስነ ስርዓት ተከብሯል፡፡ የጎንደር ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ጸሃፊ ሀሰን ደሴ (ዶ/ር) ባስተላለፉት መልእክት የአረፋ በአል የታዛዥነት የፍቅርና የአብሮነት መገለጫ የሆነ ታላቅ በዓል ነው። ይህን በዓል መንፈሳዊና ሰብዓዊ ፋይዳውን በማጉላት የተቸገሩና አቅም የሌላቸው ወገኖችን በመደገፍ፣ ፍቅራችንና አብሮነታችንን ይበልጥ በማጠናከር ማክበር አለብን ብለዋል። ሙስሊሙ ማህበረሰብ ለሰላም ለአብሮነትና ለጋራ ብልጽግና እያደረገ ያለውን ተሳትፎ አጠናክሮ መቀጠል አለበት ያሉት ደግሞ የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ናቸው፡፡ ህዝበ ሙስሊሙ ለከተማዋ እድገት የሚያደርገውን አበርክቶ እንዲያጠናክርም ጥሪ አቅርበዋል። ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል ወጣት ሷልህ ሀሚድ እንዳለው በዓሉ ሙስሊሙ ማህበረሰብ ያለው ለሌለው በማካፈል ማህበራዊና ሰብአዊ እሴቶቹን በተግባር የሚገልጥበት እለት መሆኑን ተናግሯል፡፡ አቶ መሀመድኑር ኡመር በበኩላቸው የአረፋ በዓል ሃይማኖታዊ አስተምህሮዎችን መሰረት በማድረግ ታመው አልጋ ላይ የሚገኙ አንዲሁም ጧሪና ደጋፊ የሌላቸውን ወገኖች በመደገፍ ልናከብረው ይገባል ብለዋል።   በደብረ ብርሃን ከተማ የአረፋ በዓል ላይ የከተማዋ እስልምና ጉዳይ ምክር ቤት ሰብሳቢ ዑስታዝ አህመድ መሐመድ አማን እንደገለጹት አስተዳደሩ የሙስሊሙ ማህበረሰብ የቦታና ሌሎች ጥያቄዎችን እየፈታ መሆኑን ገልጸዋል። የዛሬውን በዓል ስናከብርም ጽናትንና መንፈሳዊ መታዘዝን የምንማርበትና አስተምህሮው በሚያዘው መሰረት አቅመ ደካማ ወገኖችን በመደገፍ ሊሆን እንደሚገባም አሳስበዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት እንደገለጹት ህዝበ ሙስሊሙ የኢድ አል አድሃ በዓልን ሲያከብር የመረዳዳትና የሰላም እሴቶችን በጠበቀ መልኩ መሆን አለበት። የእምነቱ ተከታዮች ኑሩ መሀመድ (ዶ/ር) እና ወይዘሮ አይከል ሁሴን በዓሉ የአብሮነት እሴቶችን ጠብቀን፣ በመረዳዳት፣ ካለን ላይ ለሌለው አካፍለን የምናሳልፈው እለት ነው ብለዋል።  
ሕዝበ ሙስሊሙ አንድነቱን በመጠበቅ ለአብሮነት መጽናት እያበረከተ ያለውን አስተዋጾ ማጠናከር አለበት
May 27, 2026 102
ሚዛን አማን፣ ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፡-ሕዝበ ሙስሊሙ አንድነቱን በመጠበቅ ለአብሮነት መጽናት እያበረከተ ያለውን አስተዋጾ ማጠናከር እንዳለበት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ገለጸ። 1ሺህ 447ኛ የዒድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል በሚዛን አማን ከተማ አደባባይ በድምቀት ተከብሯል። በበዓሉ ላይ የተገኙት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ምክትል ሰብሳቢ ሸህ አደም መሐመድ እንዳሉት፣ የአረፋ በዓል እርስ በእርስ በመጠያየቅ የሚከበር በመሆኑ አብሮነት የሚጸናበት ነው።   በመሆኑም ለፈጣሪ በመታዘዝ ለመልካም ነገሮች መበርታት ከሕዝበ ሙስሊሙ ይጠበቃል ያሉት ምክትል ሰብሳቢው፣ ለሀገራዊ አንድነትና ሰላም መጽናት እያበረከተ ያለውን አስተዋጽኦ ማጠናከር እንዳለበትም አስገንዝበዋል። የቤንች ሸኮ ዞን እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ፀሐፊ ዑመር ሙስጠፋ በበኩላቸው የእምነቱ ሥርዓት በሚያዘው መሠረት ተካፍሎ በመብላትና በመረዳዳት የአረፋን በዓል በጋራ ማሳለፍ አለብን ብለዋል።   በዓልን በአግባቡ ማክበር የሚቻለው ሰላምና ፍቅር ሲሰፍን በመሆኑ የመቻቻል ዕሴትን በማጠናከር ለአካባቢያችን ሰላም መጽናት ከመንግስት ጋር በትብብር በመስራት ልናጠናክር ይገባል ሲሉም አክለዋል። የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር ሰለሞን ሌዊ የአረፋ በዓል አብሮነትና መደጋገፍ ጎልቶ የሚታይበት በመሆኑ ማኅበራዊ መስተጋብርን ያጠናክራል ብለዋል።   ህዝበ ሙስሊሙም ለከተማው ልማት እና እድገት ሲያደርገው የቆየውን አስተዋጽኦ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ከንቲባው ጥሪ አቅርበዋል። በእምነቱ አስተምህሮ መሰረት ለፈጣሪ በቅንነት መታዘዝና መገዛት አለብን ያሉት ደግሞ የሚዛን አማን ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሰብሳቢ እስማኤል ኑራ ናቸው።   ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል ኡስታዝ ሽኩር ጃፈር እና ወይዘሮ ጦይባ ተሬሳ በዓሉን ከጎረቤቶቻቸው እና አቅም ከሌላቸው ወገኖች ጋር በጋራ እያከበሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።   ሌሎችን እንደ ራስ መውደድና ያለንን በማካፈል በዓልን በአብሮነት ማካፈል ሃይማኖታዊ ግዴታችን በመሆኑ ይሄን በመተግበር በዓሉን እያከበርን ነው ሲሉም አክለዋል።    
የአፍሪካ ህብረት እና ኢጋድ ለኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ
May 27, 2026 188
አዲስ አበባ፤ግንቦት 19 ቀን 2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት እና የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ለ1 ሺህ 447ኛው የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሐሙድ ዓሊ ዩሱፍ በአፍሪካና በመላው ዓለም ለሚገኙ የእስልምና እምነት ተከታዮች ለኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል እንኳን አደረሳችሁ ብለዋል። ሊቀመንበሩ ባስተላለፉት መልዕክት፤ይህ የተቀደሰ በዓል የእምነት፣ የርህራሄ እና የአንድነት እሴቶች የሚንጸባረቁበት መሆኑን ገልጸዋል። እነዚህ ዕሴቶች አፍሪካ የላቀ ሰላም፣ አንድነትና ሰብአዊ ክብርን ለመገንባት ለምታከናውናቸው ተግባራት ዘላቂ መነሳሳትን እንደሚፈጥሩ አስገንዝበዋል። በተጨማሪም በዓሉ በአፍሪካ ሕዝቦች መካከል ያለውን የወንድማማችነት ትስስር ይበልጥ እንደሚያጠናክርና በአህጉሪቱ ላይ የታደሰ ተስፋን፣ ብልጽግናን እንዲሁም ስምምነትን እንደሚያሰፍን ያላቸውን ጽኑ ምኞት ገልጸዋል። በተያያዘም የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ለኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ዋና ፀሐፊው ባስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት፤ በዓሉ መሥዋዕትነት፣ ቁርጠኝነትና ደግነት የሚንጸባረቅበት በመሆኑ፤ የእነዚህን መልካም እሴቶች መንፈስ በማሰብ ሊከበር እንደሚገባ አመልክተዋል። በዓሉ ከቤተሰብ እና ከጓደኞች ጋር የሚደረግን ደስታ ይበልጥ የሚያጎላና በበረከት የተሞላ ውብ ቀን እንዲሆንም ተመኝተዋል።
በአረፋ በዓል የምናሳየውን ህብረትና አንድነትን በሌሎች የልማት ስራዎች ላይ መድገም ይገባናል - የእምነቱ ተከታዮች
May 27, 2026 75
አሶሳ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ በአረፋ በዓል የምናሳየውን ህብረትና አንድነትን በሌሎች የልማት ስራዎች ላይ መድገም ይገባናል ሲሉ የአሶሳ ከተማ የእስልምና እምነት ተከታዮች ተናገሩ። 1447ኛው የኢድ አል አድሃ አረፋ በዓል በአሶሳ ከተማ በኢድ ሶላት እና በተለያዩ ሀይማኖታዊ ክንውኖች ተከብሯል። በበዓሉ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የእምነቱ ተከታዮች የአረፋ በዓል የመረዳዳት እሴትን የሚያጎለብትና አብሮነትን የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል። ምዕመናኑ አክለውም በአረፋ በዓል የምናሳየውን ህብረትና አንድነትን በሌሎች የልማት ስራዎች ላይ መድገም ይገባናል ብለዋል።   ከታዳሚዎቹ መካከል አሰይድ አብዱራሂም እና ዩሱራ እስማኤል እንደተናገሩት፤ የአረፋ በዓል ህዝበ መስሊሙ ያለውን በማካፈል የሚያሳልፈው በመሆኑ የመረዳዳት እሴትን የበለጠ የሚያጎለብት በዓል ነው።   የበዓሉን የሶላት ስነ-ስርዓት ከሌሎች የእምነቱ ተከታዮች ጋር በጋራ ማክበራቸውን ጠቁመው፥ ይህን አንድነት በልማት ስራዎች ላይም አጠናክሮ በመቀጠል ከህዝበ ሙስሊሙ የሚጠበቀውን ኃላፊነት ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል።   ሌላው የእምነቱ ተከታዮች ሙሐመድ እስማኤል እና አሚር ናስር በአረፋ በዓል የሚከናወነውን የእርድ ስነ-ስርዓት ለሌላቸው በማካፈል በዓሉን ሁሉም የእምነቱ ተከታዮች በአንድነት እና በደስታ እንዲያሳልፉ ያደርጋል ብለዋል።   እሳቸውም ለበዓሉ በቂ ዝግጅት በማድረግ ከተቸገሩ ወገኖች ጋር ለማሳለፍ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።   የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሐጂ ሼህ ኢብራሂም ሲራጅ በበኩላቸው፤ የአረፋ በዓል ህዝበ ሙስሊሙ ለአቅመ ደካማ ወገኖች እና ረዳት ለሌላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች አለኝታነቱን የሚያሳይበት መልካም አጋጣሚ መሆኑን አመልክተዋል። በዓሉን አብሮነትን እና ወንድማማችነትን በሚያጠናክሩ ተግባራት እና ኃይማኖቱ በሚፈቅደው ልክ ማክበር እንደሚገባም አሳስበዋል።      
የኢድ አል አድሃ በዓልን በአብሮነት፣ በመረዳዳትና በመተጋገዝ መንፈስ ማክበር ይገባል
May 27, 2026 68
ሀዋሳ ፤ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፡- ህዝበ ሙስሊሙ በዓሉን በአብሮነት፣ በመረዳዳትና በመተጋገዘ መንፈስ ማክበር እንዳለበት የሀዋሳ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ሰብሳቢ ሼህ ጀማል አብዱል ሸኩር አመለከቱ። 1ሺህ 447ኛው የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል በሀዋሳ ሚሊኒየም አደባባይ በስግደት ተከብሯል። በወቅቱም የሀዋሳ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ሰብሳቢ ሼህ ጀማል አብዱልሸኩር እንዳሉት፤ ህዝበ ሙስሊሙ የኢድ አል አድሀ አረፋ በዓልን ሲያከብር በመረዳዳትና በመተጋገዝ መንፈስ መሆን አለበት።   በዓሉ የመረዳዳትና የመተጋገዝ በዓል ነው ያሉት ሼህ ጀማል ረዳት፣ ደጋፊና አጋዥ የሌላቸውን አረጋውያን፣ ህጻናትና የተቸገሩ ወገኖቻችንን በማገዝ ማክበር ይገባል ብለዋል። ለበዓሉ ከሚከናወን ዕርድ አንድ ሶስተኛውን ለተቸገሩ ወገኖች አንድ ሶስተኛውን ለጎረቤት እንዲሰጥ የዕምነቱ አስተምህሮ ያዛል ያሉት ዋና ሰብሳቢው ይህን አስተምህሮ ተግባራዊ በማድረግ በዓሉን በፍቅር፣ በሰላምና በአብሮነት እንዲያከብሩ ጥሪ አቅርበዋል።   የሲዳማ ክልል እስልምና ጉዳዮች ዋና ምክር ቤት ስራ አስፈጻሚ አባል የሆኑት ሼህ ሙክታር ሙስጠፋ በበኩላቸው በዓሉ ሰላም፣ አብሮነትና አንድነት የሚሰበክበት በዓል መሆኑን ገልጸዋል። ህዝበ ሙስሊሙ የኢድ አል አድሀ አረፋ በዓል ተረዳድቶ በደስታ የሚያከብረው በመሆኑ መላው የሀዋሳ ሙስሊም ማህበረሰብ በዕምነቱ አስተምህሮ መሰረት በዓሉን በመረዳዳትና በመተጋገዝ በሰላም እንዲያከብር ጥሪ አቅርበዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት ወይዘሮ አይሻ አህመድ እንዳሉት እስልምና እንደሚያዘው በዓሉን ረዳት ከሌላቸውና ከጎረቤቶቻቸው ጋር በጋራ ለማክበር ተዘጋጅተዋል። ከዚህ ባለፈ በዙሪያችን ከሚገኙ የሁሉም ዕምነት ተከታዮች ጋር በመሆን በመጠያየቅና በመረዳዳት እናከብረዋለን ብለዋል።   ሌላው የበዓሉ ታዳሚ ሀጂ ሀሺም ሁሴን በበኩላቸው በዓሉን ከጎረቤቶቻቸው ጋር በመሆን በጋራ ለማክበር መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።
ትምህርት ለትውልድ
May 27, 2026 95
ቴክኖሎጂ በረቀቀበት በዚህ ዘመን ያለ ትምህርት ሁለንተናዊ ብልፅግናን ማረጋገጥ እንደማይቻል በመገንዘብ መንግስት ዘርፉን የማኀበረሰብ የወል ትርክት መፍጠሪያና የሀገር ዘላቂ ዕድገት ማስቀጠያ ድልድይ አድርጎ ወስዶታል። መንግሥት ሁለንተናዊ ብቃት ያላቸውን ዜጎች በማፍራት የሀገሪቱን የነገ ተስፋ ለማለም ትምህርትን እንደ ቁልፍ መሣሪያ እየተጠቀመበት ይገኛል። በዚህም መሠረት ላለፉት አምስት ዓመታት በትምህርት ጥራትና አግባብነት ላይ የታዩ ስብራቶችን ለመጠገን ሰፊ የለውጥ መርሃ ግብሮች ተተግብረዋል። ለ28 ዓመታት የቆየውን ፖሊሲ በመቀየር፣ አዲስ የትምህርትና ሥልጠና ፍኖተ-ካርታን መሠረት ያደረገ ፖሊሲ ወደ ትግበራ እንዲገባ ተደርጓል። ይህም ለመጀመሪያ ጊዜ የአጠቃላይ ትምህርት አዋጅና የብቃት ማእቀፍ ሥርዓት እንዲዘረጋ በማድረግ ረገድ ትልቅ ምዕራፍ ከፍቷል። ባለፉት ዓመታት ከተመዘገቡ ስኬቶች መካከል የ"ትምህርት ለትውልድ" ንቅናቄን በመፍጠር የትምህርት ቤቶችን ደረጃ የማሻሻልና የመሠረተ ልማት ግንባታን የማፋጠን ሥራ ተጠቃሽ ነው። በተለይም ዓለም አቀፍ አድናቆት ያተረፈው የትምህርት ቤት ምገባ መርሃ ግብር፣ ከ1 ነጥብ 7 ሚሊዮን ወደ 8 ሚሊዮን ተማሪዎች እንዲያድግ ተደርጓል። ይህ ተግባር የተማሪዎችን ትምህርት የማቋረጥ ምጣኔ ከመቀነሱም በላይ ለወላጆች ትልቅ እፎይታን ሰጥቷል። በዲጂታል ዘርፍም "ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025" አጀንዳን መሠረት በማድረግ የዲጂታል ትምህርት ስትራቴጂ ተቀርጾ በርካታ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በኮምፒውተር ላብራቶሪና በኢንተርኔት እንዲገናኙ ተደርጓል። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ጥራት ለማረጋገጥም ዩኒቨርሲቲዎች በተልዕኮ እንዲለዩና ወደ ራስ-ገዝነት እንዲሸጋገሩ የሚያስችል ሥርዓት ተዘርግቷል። የመውጫ ምዘና (Exit Exam) ተግባራዊ መደረጉም የተመራቂዎችን ብቃት ለማረጋገጥ የተወሰደ ቁልፍ እርምጃ ነው። መንግሥት ትምህርትን ከንድፈ ሐሳብ ወደ ተጨባጭ ተግባር ለመቀየር ሀገር በቀል ዕውቀትን በሥርዓተ-ትምህርቱ ውስጥ አካቷል። ባለፉት አምስት ዓመታት ከ34 ሺህ በላይ የመዋዕለ ሕፃናት ግንባታዎች የተከናወኑ ሲሆን፣ የቅድመ-መደበኛ ትምህርት ተሳትፎን ከ36.7% ወደ 59.8% ማሳደግ ተችሏል። በተጨማሪም ከ17,500 በላይ አዳዲስ ትምህርት ቤቶችና ከ38 ሺህ በላይ ተጨማሪ ክፍሎች ተገንብተዋል። በትምህርት ተደራሽነት ረገድ አሁን ላይ 27 ሚሊዮን የሚጠጉ የአጠቃላይ ትምህርትና ከ828 ሺህ በላይ የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎች በትምህርት ገበታ ላይ ይገኛሉ። በቀጣይ ዓመታት የቅድመ-አንደኛና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ተሳትፎን 100% ለማድረስ ታልሟል። የልዩ ፍላጎት ተማሪዎች የድጋፍ መስጫ ማዕከላትን ቁጥር ወደ 2,150 ለማሳደግና የተማሪ-ክፍል ጥምርታን በአንደኛ ደረጃ 1 ለ 50፣ በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ 1 ለ 40 ለማድረግ በትኩረት ይሠራል። የወደፊቱ ትኩረት "ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ላይ በማድረግ ሰው ሠራሽ አስተውሎትን (AI) በትምህርት ሥርዓቱ ውስጥ ለማስፋፋት ዝግጅቶች ተጠናቀዋል።
በዓሉ ያለው ለሌለው በማካፈል ሁሉም እኩል በደስታ የሚያሳልፈው ነው
May 27, 2026 66
መቱ/ጅማ ፤ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ) - የኢድ አል አድሃ (አረፋ) የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል ያለው ለሌለው በማካፈል ሁሉም እኩል በደስታ የሚያሳልፈው በዓል ነው ሲሉ በመቱ እና ጅማ ከተሞች የሚገኙ የእምነቱ ተከታዮች ገለጹ። የዘንድሮው 1447ኛው የኢድ አል አድሃ (አረፋ) በዓል የአደባባይ ሰላት ፕሮግራም በመቱ እና በጅማ ከተሞች በደማቅ ሁኔታ ተከናውኗል። በመቱ ከተማ በተካሄደው የበዓል ሥነ ሥርዓት ላይ የተሳተፉት አቶ ሚስባው ደጋጋ እንደገለጹት፤ በዓሉ ያለው ለሌለው በማካፈል ሁሉም እኩል በደስታ እንዲያሳልፍ የሚያዝ የእምነት መርሕ አለው።   እርሳቸውም ይህንን መሠረት በማድረግ ሌሎችን በመርዳት እያከበሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ አቶ መሐመድጣሂር አባገሮ በበኩላቸው፣ የኢድ አል አድሃ አረፋ በዓል የመረዳዳትና የመደጋገፍ በዓል መሆኑን ጠቅሰው፣ በዓሉን ከሌሎች የእምነት ተከታዮች ጋር ጭምር በአብሮነት እያሳለፉት እንደሚገኝ ለኢዜአ ገልጸዋል።   የመቱ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሰብሳቢ ሼህ ኤልያስ መሐመድ በበኩላቸው ባስተላለፉት መልዕክት የአረፋ በዓል የመረዳዳትና የአብሮነት እሴቶቻችንን ይበልጥ አጠናክረን የምናስቀጥልበት ነው ሲሉም ገልጸዋል። ከሌሎች እምነት ተከታይ ወንድሞቻችን ጋር በአብሮነት እና በወንድማማችነት በማክበር የበዓሉን እሴት ማጎልበት ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል።   በተመሳሳይ ሁኔታ በጅማ ከተማ እየተከበረ በሚገኘው በዓል ላይ የከተማው የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሰብሳቢ ሼክ መሀመድ አሚን ተማም፤ ሀገር ሰላምና እድገቷ ቀጣይነት የሚኖረው ስለ ሰላም በተግባር ስንሰራ በመሆኑ፣ ከሚያለያዩን ይልቅ አንድ የሚያደርጉንን ጉዳዮች ማስቀደም ይኖርብናል ብለዋል። የበዓሉ ታላቅ መልዕክት ሰላምና መተሳሰብ በመሆኑ፣ አቅመ ደካሞችን በመርዳትና አንዱ ሌላውን በመምከር ለሀገር አንድነት ዘወትር መስራት ይገባል ነው ያሉት።   የጅማ ከተማ የበዓሉ ታዳሚ ሀሊማ አብዱልባሲጥ በበኩሏ የሀገር ማደግ በመተሳሰብና በማካፈልም ጭምር ነው ብላለች። ይህ ደግሞ በበዓላት ወቅት ብቻ ሳይሆን በቀጣይነትም ሊደረግ ይገባል ስትልም አስገንዝባለች። በተግባር ለሀገር መስራት ማለት በየትኛውም ጊዜ ሰላምን ማስቀደም ነው ያሉት ደግሞ አቶ አብዶ ከማል እና አዩብ አብዱልከሪም ናቸው።   ዘወትር ለሰላምና ለመልካም ነገር በመትጋት ሀገርን መቀየር እንደሚቻል የገለጹት አስተያየት ሰጪዎቹ፣ ከበዓሉ ቀደም ብለው ለአቅመ ደካሞች የሚሆን ድጋፍ ሲያሰባስቡና ሲያዘጋጁ እንደነበርና ይህንንም በጎ ተግባር ከበዓሉ በኋላም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስረድተዋል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም