ቀጥታ፡
ማህበራዊ
ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ተጋላጭነት ለመቀነስ ከአጋር አካላት ጋር የተቀናጀ ሥራ እየተከናወነ ነው
Feb 26, 2026 35
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ተጋላጭነት ለመቀነስ ከአጋር አካላት ጋር የተቀናጀ ሥራ እያከናወነ እንደሚገኝ ጤና ሚኒስቴር ገለጸ፡፡ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በካንሰር ምርምር ላይ የሚያተኩረውን የelse korner center fore cancer care (EKC 2) ፕሮጀክት የመጀመሪያ ምዕራፍን በመጠናቀቅ ሁለተኛውን ምዕራፍ ይፋ አድርጓል፡፡   ይፋ የተደረገው ፕሮጀክት ለቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የሚተገበር ሲሆን የሴቶችን የካንሰር ሕክምና አገልግሎት በየአካባቢው ተደራሽ ማድረግ፣ ስለ ጡት እና ማህፀን በር ካንሰር ግንዛቤን ማሳደግ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በጤና ሚኒስቴር የበሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር መሪ ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ሕይወት ሰለሞን በዚሁ ወቅት፤ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ከመከሰታቸው በፊት በቅድመ ጥንቃቄ መከላከል ይቻላል ብለዋል፡፡ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች በሰዎች ላይ የሚያስከትሉትን ማኅበራዊ፣ ስነ-ልቦናዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጫናዎች ለመግታት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል፡፡ መንግስት የበሽታዎቹን ስርጭት ለመግታት ከግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች ባሻገር ሌሎች ውጤታማ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ጠቁመው ህብረተሰቡ የሚያደርገውን ጥንቃቄ ማጠናከር ይገባል ብለዋል፡፡   የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ የካንሰርና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ምርምር ክፍል አስተባባሪ ዶክተር አዳሙ አዲሴ በበኩላቸው፤ የካንሰር በሽታ በአፍሪካ ደረጃ አሳሳቢነቱ እየጨመረ መምጣቱን ጠቁመዋል። ይህንን ለመቅረፍ ኮሌጁ ችግር ፈቺ በሆኑ ምርምሮች ላይ ትኩረት አድርጎ እየሰራ መሆኑንና የኤልሳ ክሮነር የካንሰር ሕክምና ማዕከል ፕሮጀክትም የዚሁ አካል መሆኑን ገልጸዋል።   የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ የጤና ማጎልበትና በሽታ መከላከል ዳይሬክተር አቶ ጌቱ ቢሳ እንደገለጹት፣ ፕሮጀክቱ በተለይ በእናቶች ላይ የሚከሰቱ የጡትና የማህፀን በር ካንሰር ለመቀነስ ትልቅ ሚና አለው። ቀደም ሲል በተመረጡ ሆስፒታሎች ብቻ ይሰጥ የነበረው አገልግሎት አሁን በፕሮጀክቱ አማካኝነት ወደ ጤና ጣቢያዎች ዝቅ እንዲል መደረጉንም ጠቅሰዋል፡፡
በድሬደዋ የባህላዊ ፍርድ ቤቶች ተደራሽነትና አገልግሎቶች ይጠናከራሉ - ከንቲባ ከድር ጁሃር
Feb 26, 2026 77
ድሬደዋ፣ የካቲት 19/2018(ኢዜአ):- በድሬደዋ ለተገልጋዩ ፈጣንና ተደራሽ የፍርድ አገልግሎት በመስጠት ወሳኝ ሚና እያበረከቱ የሚገኙ ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ይጠናከራሉ ሲሉ የአስተዳደሩ ከንቲባ ከድር ጁሃር ተናገሩ። በድሬደዋ አስተደዳር የባህላዊ ፍርድ ቤቶች ምክርቤት የማቋቋምና ለባህላዊ ፍርድ ቤቶች ዕውቅና የመስጠት ስነስርአት ዛሬ በይፋ ተካሂዷል።   በስነስርዓቱ ላይ የተገኙት የአስተዳደሩ ከንቲባ ከድር ጁሃር በወቅቱ እንዳሉት፤ ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ለዜጎች ተደራሽ አገልግሎት በመስጠት የመደበኛ ፍርድ ቤቶችን ጫና እያቃለሉ ናቸው። የፍትህ አገልግሎቱ እንዲሻሻል እያከናወኑ ያሉትን አበረታች ተግባራት ይበልጥ ተቋማዊ ለማድረግ የሚመሩበት የህግ ማዕቀፍ በአስተዳደሩ ምክርቤት ፀድቆ ወደ ስራ መገባቱንም አስታውሰዋል። በመሆኑም ባህላዊ ፍርድ ቤቶቹ ውጤታማ ስራ እንዲያከናውኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው የምክርቤቱ መቋቋም ወሳኝ እርምጃ ነው ብለዋል ።   የድሬደዋ አስተዳደር ፍትህ፣ ፀጥታና የህግ ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱሰላም አህመድ በበኩላቸው የባህላዊ ፍርድ ቤቶች የሚከተሉት የአሰራር ስነስርአት ማህበረሰቡን ተደራሽ በማድረግ የፍትህ አገልግሎት እንዲያገኝና ማህበራዊ መስተጋብር እንዲጠናከር እያስቻሉ መሆኑን አንስተዋል። ከመደበኛ ፍርድ ቤቶች የሚለያቸውን ድንበርና አሰራር በመለየት የሚፈለገውን ውጤታማ ስራ እንዲያከናውኑ አስፈላጊው ድጋፍና እገዛ እንደሚደረግላቸው በማስታወቅ። የባህላዊ ፍርድ ቤቶች ባህላዊ ህጎችና እሴቶችን በመጠበቅና የማህበረሰቡን መስተጋብር በማጠናከር የመደበኛ ፍርድ ቤቶችን የስራ ጫና እያቃለሉ መሆናቸውን የገለፁት ደግሞ የድሬደዋ አስተዳደር የይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቶች ፕሬዚዳንት አቶ ነጂብ ኢድሪስ ናቸው።   በተጨማሪም የሃብትና የጊዜ ብክነትን በመከላከል ምርታማነት ይበልጥ እንዲጎለብት አስተዋፅኦ እያበረከቱ መሆኑን ጠቅሰው ዛሬ የተሰጣቸው ዕውቅና በቀጣይ የተሻለ ስራ ለመስራት እንደሚያስችላቸው ነው አቶ ነጂብ የተናገሩት።   የኃይማኖት አባቶችና ታዋቂ የአገር ሽማግሌዎች፣ አባገዳዎችና ኡጋዞች፣ በየደረጃው የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች የተመሰረተው የባህላዊ ፍርድ ቤት ምክርቤት አባላት መሆናቸውን በስነስርዓቱ ላይ ተመልክቷል።
ለብሔራዊ ጥቅም መቆም ለዘመናት የቆየ የአብሮነትና የሀገር ፍቅር ውጤት ነው
Feb 26, 2026 62
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ ለብሔራዊ ጥቅም መቆም ለዘመናት የዳበረ የአብሮነትና የሀገር ፍቅር ውጤት ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ሊዲያ ግርማ ገለጹ። 130ኛ የአድዋ ድል በዓል አስመልክቶ፣ "ከአኩሪ ታሪክ ወደ ብሩህ አድማስ" በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ የፓናል ውይይት ተካሂዷል።   በዚህ ወቅት ቢሮ ሀላፊዋ እንደተናገሩት የአድዋ ድል የሀገራችንን ዕጣ ፈንታ የሚቀይር፣ አንድነቷ የጸና እና የበለፀገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የሚያነሳሳ ነው። የታላቁ የህዳሴ ግድብ መጠናቀቅም የዚሁ "ዳግማዊ አድዋ" ህያው ማሳያ እንደሆነና ለሌሎች ሁለንተናዊ ስኬቶች መነሳሳት እንደሚሆን ተናግረዋል። የዘንድሮው 130ኛው የአድዋ ድል በዓል በዋናነት በይቻላል መንፈስ ውጤቶቻችንን እና መልካም ገጽታችንን ለዓለም ያሳየንበት፣ በንጋት ሃይቅና በጉባ ተራሮች ላይ የብልጽግና ብስራቶችን ያወጅንበት እና 7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የሚከናወንበት ወቅት ላይ መሆናችን ልዩ ያደርገዋል ብለዋል።   በውይይቱ ላይ "የአድዋ አደራ አንድነት፣ ሉዓላዊነትና ማንሰራራት!" በሚል የመወያያ ሰነድ መቅረቡን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ጽህፈት ቤት አስታውቋል።   በመድረኩ የመከላከያ ሰራዊት የዘመቻ ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጀነራል በላይ ስዩም፣ የአድዋ ድል በዓል የነጻነት ተምሳሌት በመሆኑ ትውልዱ ታሪኩን ጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ ማስተላለፍ አለበት ብለዋል። የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው ባስተላለፉት መልዕክት የህዳሴው ግድብ ዳግማዊ አድዋ ነው ሲሉ ገልጸዋል።
የጤና ጣቢያ ግንባታው የሕክምና አገልግሎት ለማግኘት የሚደረግን የረጅም ርቀት ጉዞን አስቀርቷል - ነዋሪዎች
Feb 26, 2026 57
መተማ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በቀበሌያቸው የጤና ጣቢያ ተገንብቶ ለአገልግሎት በመብቃቱ ወደ ሌሎች አካባቢዎች የሚያደርጉትን የጉዞ እንግልትና ወጪን እንዳስቀረላቸው በምዕራብ ጎንደር ዞን የመተማ ወረዳ ነዋሪዎች ገለጹ። ጥራቱን የጠበቀ የሕክምና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የጤና ተቋማትን ደረጃ ማሻሻል ቁልፍ ተግባር ነው የጤና ጣቢያ ግንባታው ለሕክምና አገልግሎት ረጅም ርቀት መጓዝን ከማስቀረት ባለፈ ጊዜና ጉልበታቸውን ለልማት እንዲያውሉ እንዳገዛቸውም ነዋሪዎቹ አመልክተዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን መተማ ወረዳ የኩመር አፍጥጥ ቀበሌ ነዋሪዎች፣ በአቅራቢያቸው በተገነባው ጤና ጣቢያ ተገቢውን የሕክምና አገልግሎት ማግኘት መጀመራቸውን ገልጸዋል።   ቀደም ሲል ለሕክምና አገልግሎት ወደ ገንዳ ውኃ ከተማ ይሄዱ እንደነበር አስታውሰው፣ ይህም ለከፍተኛ ወጪና እንግልት ዳርጎናል ብለዋል። የቀበሌው ነዋሪ አየሁሽ ስመኘው እንደገለጹት፣ የጤና ጣቢያው በአቅራቢያቸው መገንባቱ ያለምንም እንግልት ፈጣን ሕክምና እንዲያገኙ ረድቷቸዋል። ቀደም ሲል ወደ ገንዳ ውኃ በመሄድ ይባክን የነበረ ጊዜና ገንዘብን በመቆጠብ ለልማት ሥራ ማዋል መቻላቸውን ተናግረዋል። ሌላዋ ነዋሪ ስፍራሽ ጌጡ የጤና ጣቢያው ግንባታ የእናቶችና ህጻናትን ጤና ከማሻሻል አኳያ ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። በጤና ጣቢያው የሕፃናት የተመጣጠነ ምግብ ዝግጅትን አስመልክቶ የሚሰጠው ትምህርት ለህጻናት ጤናና ለተሻለ ዕድገት ከፍተኛ ሚና እንዳለውም ገልጸዋል።   የምዕራብ ጎንደር ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ ጅብሪል መርሻ፣ በዞኑ ካሉት 23 የጤና ተቋማት መካከል ዘንድሮ ግንባታቸው ተጠናቆ ወደ ሥራ ከገቡት ሁለቱ ጤና ጣቢያዎች አንዱ የአፍጥጥ ጤና ጣቢያ መሆኑን ገልጸዋል። ጤና ጣቢያው ከሌሎች የሕክምና አገልግሎቶች በተጨማሪ ከ120 በላይ ለሚሆኑ የሥነ-አእምሮ ሕሙማን ተገቢው ሕክምና መስጠቱንም ገልጸዋል። ዞኑ ሰፊ የእርሻ ኢንቨስትመንት የሚካሄድበት እንደመሆኑ የነዋሪውንና የሠራተኛውን ጤና መጠበቅ ለምርታማነት ዕድገት ወሳኝ ነው ብለዋል።
በኢትዮጵያ የተጀመረው ሰው አልባ የፖሊስ አገልግሎት ሁነቶችን በስኬት ማስተናገድ የሚያስችል አቅም ፈጥሯል
Feb 26, 2026 81
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአፍሪካ የመጀመሪያውን የሰው አልባ /Smart/ የፖሊስ ጣቢያ አገልግሎትን በማስጀመር ዓለም አቀፋዊ እና አህጉራዊ ሁነቶችን በስኬት የማስተናገድ አቅም መፍጠሯን የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አዛዥ ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተያዘው የካቲት ወር የመጀመሪያ ሳምንት ዜጎች የፖሊስ አገልግሎትን በቴክኖሎጂ ታግዘው በተሻለ ፍጥነት የሚያገኙበት ሰው አልባ የፖሊስ አገልግሎት ማስጀመራቸው ይታወቃል፡፡ ሰው አልባ የፖሊስ አገልግሎት ተገልጋዩ በቴክኖሎጂ ታግዞ ራሱን በራሱ በማስተናገድ ተደራሽ፣ ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘት የሚያስችለው መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ አገልግሎቱ የወንጀል አቤቱታዎችን ለማቅረብ፣ የትራፊክ አደጋዎችን ሪፖርት ለማድረግ፣ የትራፊክ ቅጣቶችን ለመክፈል የጠፉና የተገኙ ቁሳቁሶችን ለማሳወቅ እንዲሁም የቱሪስት ደህንነት አገልግሎት ለማግኘት ወሳኝ ሚና አለው ነው ያሉት፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አዛዥ ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ በዘመናዊ መልክ ከተቋቋመ 117 ዓመታትን ያስቆጠረ በአፍሪካ አንጋፋው ተቋም ነው፡፡ ከአንጋፋነቱ ባለፈ እንደ የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንትና የጸረ አፓርታይድ ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ ያሉትን በማሰልጠን ለአፍሪካ የነፃነት ትግል ሚናውን የተወጣ፤ በቀጣናው ሰላምና ደህንነት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገ የሚገኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከለውጡ ወዲህ የተደረገው ሪፎርም በሰለጠነና ብቁ የሰው ሀይል የተሟላ፣ ዘመኑ ያፈራቸውን ቴክኖሎጂዎች የታጠቀና በሎጂስቲክስ አቅሙ የዳበረ ተቋም መፍጠር ተችሏል ብለዋል፡፡ በዓለም የተሻለ የፖሊስ አገልግሎት አፈጻጸም ካላቸው ሀገራት ተርታ ለመሰለፍ ሪፎርም መደረጉን በማንሳት፤ በተለያዩ ዘርፎች እስከ ሶስተኛ ዲግሪ/ፒ ኤች ዲ/ የሚያስተምሩ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን መገንባቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህም እስካሁን በነበሩት ትላልቅ የፖሊስ ሥምሪቶች ተጨባጭ ውጤቶች በማስመዝገብ አንጋፋነቱን በተግባር አሳይቷል ነው ያሉት፡፡ ኢትዮጵያ በተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት በሰላም ማስከበር ተልዕኮ በመሰማራት አንቱታን ያተረፈ ስኬት በማስመዝገብ ለዓለም ሰላምና ደህንነት ሚናዋን እየተወጣች መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የተጀመረው የሰው አልባ የፖሊስ አገልግሎት የውጭና የሀገር ውስጥ ዜጎች በቴክኖሎጂ የታገዘ የፖሊስ አገልግሎት እንዲያገኙ እንደሚያስችልና የተጠቃሚዎችን የመረጃ ደህንነትና ምስጢራዊነት ለመጠበቅ የላቀ ቴክኖሎጂ እንደሚጠቀምም ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ የፈጠረው ብቁ የሰው ሃይል፣ የታጠቀው ዘመናዊ ቴክኖሎጂ እና የተሟላ ሎጂስቲክስ ዓለም አቀፋዊና አህጉራዊ ሁነቶችን በስኬት ለማጠናቀቅ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል፡፡
በዓድዋ የተገኘውን አንጸባራቂ ድል ሀገራዊ የልማት ግቦችን በማሳካት መድገም ይገባል 
Feb 26, 2026 94
ሐረር ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በዓድዋ የተገኘውን አንጸባራቂ ድል ትውልዱ አንድነቱን የበለጠ በማጠናከርና ሀገራዊ የልማት ግቦችን በማሳካት ሊደግመው እንደሚገባ የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር ተናገሩ። 130ኛው የዓድዋ ድል በዓል በሐረሪ ክልል ደረጃ በፓናል ውይይት ተከብሯል፡፡ አያቶቻችን በጠንካራ አንድነትና መስዋዕትነት ሉዓላዊ ሀገር እንዳስረከቡን ሁሉ ትውልዱም ተባብሮ ሀገሩን ማበልጸግ ይጠበቅበታል የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር በወቅቱ እንደገለጹት፤ የዓድዋ ድል በኢትዮጵያውያን የጋራ ትግል የተገኘ አንጸባራቂ ድል ነው።   የኢትዮጵያውያን አይበገሬነት የተረጋገጠበት የአንድነት ውጤት መሆኑን ገልጸው፣ የአሁኑ ትውልድም አንድነቱን በማጠናከር ሀገራዊ የልማት ግቦችን ለማሳካት መረባረብ አለበት ብለዋል። በበዓሉ የተገኙት በሀገር መከላከያ ሰራዊት የምስራቅ እዝ ጠቅላላ አገልግሎት ሃላፊ ኮሎኔል ሀሰን ሰዒድ በበኩላቸው፤ የዓድዋ ድል ለመላው አፍሪካውያን ጥቁር ህዝቦች ኩራት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የዓድዋ ድል እየተከበረና እየተዘከረ የመጣ አኩሪ ታሪክ መሆኑን ገልጸው፤ ለወደፊቱም የመላው ጥቁር ህዝቦች ኩራት ሆኖ ይቆያል ብለዋል። ድሉ በመላው የሀገሪቱ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች የተባበረ ክንድ የተመዘገበ ነው ያሉት ኮለኔል ሀሰን ድሉን ሀገራዊ ልማትና ብልጽግናን በማረጋገጥ ማክበር ይገባል ብለዋል።   እንዲሁም የኢትዮጵያን ክብርና ሉዓላዊነት በማስከበርና ሌሎች በሀገሪቱ ላይ የሚቃጣን ማንኛውንም ትንኮሳ በመመከት በጋራ በመቆም ማክበር ይገባል ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል። በፓናል ውይይት በተከበረው በዓል ላይ የመከላከያ ሰራዊት መኮንኖች፣ የፌዴራልና የክልሉ ፖሊስ አባላትና ሌሎች የጸጥታ አካላት፣ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የቀድሞ የጦር አባላትና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
ዓድዋ የኢትዮጵያውያን የአንድነት ካስማና የማይደበዝዝ የታሪክ አሻራ ነው
Feb 26, 2026 48
ባህር ዳር፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ ዓድዋ የኢትዮጵያውያን የአንድነት ካስማና የማይደበዝዝ የታሪክ አሻራ መሆኑን የአማራ ክልል የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ሊቀመንበር ዳኝነት አያሌው ገለጹ። በዓድዋ ድል ጀግኖች አባቶች ያሳዩትን ጥንካሬና አንድነት ወጣቱ ትውልድ በልማት ሊደግመው ይገባል የዓድዋ ድል የኢትዮጵያውያን የጋራ መስዋዕትነት ውጤት ብቻ ሳይሆን፣ ለመላው ጥቁር ሕዝቦችና ለአፍሪካውያን የነጻነትና የኩራት አርማ ነው። ኢትዮጵያውያን የሀገራቸውን ሉዓላዊነትና ዳር ድንበር ለማስጠበቅ ያለምንም ልዩነት ድል ማድረጋቸው በቅኝ ግዛት ሥር ለነበሩ አፍሪካውያን ትልቅ ስነ-ልቦናዊ ስንቅ ሆኗል። የአማራ ክልል የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማሕበር ሊቀመንበር ዳኝነት አያሌው ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፣ ኢትዮጵያውያን የሀገራቸው ክብር ሲደፈር በራሳቸው ስንቅና ትጥቅ መዝመታቸውን አስታውሰዋል። ዓድዋ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች ክንዳቸውን አስተባብረው የቅኝ ገዥዎችን የባርነት ቀንበር የሰበሩበት ታሪካዊ ድል መሆኑንም ጠቁመዋል። ድሉ ለኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን፣ ለመላው የጥቁር ሕዝቦች የነጻነት ፋና ወጊ መሆኑንና የኢትዮጵያውያን የአንድነት ካስማና የማይደበዝዝ የታሪክ አሻራ መሆኑንም ነው ያብራሩት። የሀገርን አንድነት ለማጽናት ስለ ቀደመ ታሪክ ማወቅና ታሪኩን ማስቀጠል ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው የዓድዋ ጀግኖች አባቶች በደማቸው ያቆዩትን ሀገር፣ የአሁኑ ትውልድ በዕውቀትና በሥራ በመትጋት የተሻለ ሀገር መገንባት ይጠበቅበታል ነው ያሉት። የዓድዋ ድል ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ክብር ከፍ ያደረገና የአፍሪካውያን የአንድነትና የሉዓላዊነት ምልክት ሆኖ ይጠቀሳል።
ሴቶች በተለያየ መስክ ያላቸውን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Feb 26, 2026 78
ሰመራ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- የሴቶችን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያመጡ መሆናቸውን የብልፅግና ፓርቲ ሴቶች ክንፍ ምክር ቤት አባል ወይዘሮ ተስፋነሽ አበራ ተናገሩ። በዞኑ በጤና ጣቢያዎች ደረጃ መሰጠት የጀመረው በቀዶ ሕክምና የማዋለድ አገልግሎት የእናቶችና ህጻናትን ጤና ለማሻሻል አግዟል በብልጽግና ፓርቲ የአፋር ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የሴቶች ክንፍ አስተባባሪነት "በሴቶች ተሳትፎ የፀናችና የበለፀገች ኢትዮጵያ" በሚል መሪ ሐሳብ የሴቶች ንቅናቄ መድረክ እያካሄደ ነው።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልና በብልፅግና ፓርቲ የሴቶች ክንፍ ምክር ቤት አባል ወይዘሮ ተስፋነሽ አበራ፤ፓርቲው የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ያከናወናቸው ተግባራት ስኬታማ ናቸው ብለዋል።   ሴቶች እንደ ሀገር በመጣው ለውጥ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልፀው ፓርቲው ውስብስብ የሆኑ ማነቆዎችን በመሻገር እመርታዊ ድሎችን ማስመዝብ መቻሉንም ተናግረዋል። በተለይም ዕድሎችን አሟጦ በመጠቀም ሴቶችን በኢኮኖሚ፣ ማህበራዊና ፓለቲካዊ እንቅስቃሴ ውስጥ በማሳተፍ የሚታዩ ውጤቶችን ማስመዝገብ መቻሉንም ነው የጠቀሱት። በብልፅግና ፓርቲ የአፋር ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መሐመድ ሁሴን በበኩላቸው ያለ ሴቶች ተሳትፎ የሚሳካ አንዳችም ተግባር እንደሌለ በማመን የሴቶችን ተሳታፊነት ከመቼውም ጊዜ በላይ ማሳደግ ተችሏል ነው ያሉት።   የዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሚናቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል። በአፋር ክልል የሚገኙ የሴቶች አደረጃጀቶችን በመጠቀም በየደረጃው ተጠቃሚ እንዲሆኑ የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን የተናገሩት ደግሞ በብልፅግና ፓርቲ የአፋር ክልል ሴቶች ክንፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ ኡርቲያይ ያይሶ ናቸው።  
አያቶቻችን በጠንካራ አንድነትና መስዋዕትነት ሉዓላዊ ሀገር እንዳስረከቡን ሁሉ ትውልዱም ተባብሮ ሀገሩን ማበልጸግ ይጠበቅበታል
Feb 26, 2026 51
ድሬደዋ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- አያቶቻችን በመስዋዕትነት ሉዓላዊ ሀገርን እንዳስረከቡን ሁሉ ትውልዱም ወደ ብልጽግና የተሻገረች ሀገርን ለቀጣዩ ለማውረስ በቁርጠኝነት መትጋት አለበት ሲሉ የድሬዳዋ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የታሪክ መምህራን ተናገሩ። የዓድዋ ድልን አስመልክተው የድሬደዋ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የታሪክ መምህራን ሄኖክ ሲማ እና ገብረ መድህን ታደሰ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የዓድዋ ድል ኢትዮጵያ ለጥቁር ህዝቦች ነፃነት ችቦ የለኮሰችበት ዘመን የማይሽረው ደማቅ ታሪክ ነው።   የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን በጋራ ቆመው የሀገር ክብርና ሉዓላዊነት ያስጠበቁበት የመላ ጥቁር ህዝቦች የአሸናፊነት ምልክት ነው በአያቶች የተመዘገበውን ደማቅ ታሪክ ትውልዱ የትኛውንም መስዋዕትነት በመክፈል ሊጠብቀው እንደሚገባም አስገንዝበዋል።   የዓድዋን ህያው ታሪክ በአግባቡ እየተማረ የሚገኘው አገር ገንቢውና ተረካቢው ትውልድ በአገር መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ ህብረ ብሔራዊ አንድነትን ማፅናት እና በጋራ መቆም ያለውን ወሳኝ ሚና በአግባቡ እየተረዳ መሆኑን አንስተዋል። የአባቶቹን ወኔ በመላበስ በአንድነት ድህነትንና ልመናን ከአገር ለማጥፋት የተጀመረውን ጉዞ በማሳካት የራሱን ተሻጋሪ ታሪክ መፃፍ እንዳለበት ነው ያስገነዘቡት ።
ወራቤ ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ከ60 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የህክምና ግብዓት ድጋፍ ተደረገለት
Feb 26, 2026 64
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ ወራቤ ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ከ60 ሚሊየን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያለው የህክምና ግብዓት ድጋፍ ተደረገለት፡፡ ድጋፉን ያደረገው ኦርፋንስ ኢንኒድ ዩኤስኤ /Orphans In Need USA/ የተሰኘ ግብረሰናይ ድርጅት ሲሆን ድጋፉ በኡስታዝ አቡበከር አህመድ በኩል የተገኘ መሆኑም ታውቋል፡፡ የህክምና ግብዓቱ ለተለያዩ ህክምና አገልግሎቶች የሚውልና ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን የሆስፒታሉ ስራ አስኪያጅ ዶክተር ካሊድ ሸረፋ ገልጸዋል፡፡ የህክምና ግብዓቱ ከአንድ ሺህ በላይ አይነት እንደ ጠቅላላ ቀዶ ህክምና፣ የአጥንት ህክምና፣ የእናቶችና ህጻናት እና ሌሎች ህክምናዎች እንደሚውል ተገልጿል።   ድጋፉ ከስልሳ ሚሊየን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ እንዳለውም የፋርማሲ ዳይሬክተሩ ሀቀዲን ከድር ገልጸዋል፡፡ የወራቤ ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የማኔጅመንት አባላትና ሌሎች የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት የህክምና ግብዓቱ ርክክብ ተከናውኗል። በዚህ ወቅት የሆስፒታሉ ስራ አስኪያጅ ዶክተር ካሊድ ሸረፋ እንደገለጹት ግብዓቱ ከፍተኛ ዋጋ የሚያወጣ ለተለያዩ የህክምና አገልግሎቶች የሚውልና ህይወት አድን የሚባሉ ግብዓቶችን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። ድጋፉን ላደረገው ኦርፋንስ ኢንኒድ ዩኤስኤ/Orphans in Need USA/ እና ለኡስታዝ አቡበከር አህመድ ምስጋና አቅርበዋል። መሰል ድጋፎችን ማድረግ በቀጥታ የዜጎች ህይወት ላይ ለውጥ የሚያመጣ በመሆኑ ሆስፒታሉ ታካሚዎችን የተሻለ ለማገልገል የሚደረጉ መሰል ድጋፎችን ያበረታታል ብለዋል፡፡
በአማራ ክልል የማህበራዊ ተቋማትን ደረጃ በማሻሻል ለህብረተሰቡ የተሻለ አገልግሎት እንዲሰጡ እየተደረገ ነው - ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር)
Feb 25, 2026 132
ደሴ፤ የካቲት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የማህበራዊ ተቋማትን ደረጃ በማሻሻል ለህብረተሰቡ የተሻለ አገልግሎት እንዲሰጡ እየተደረገ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) ገለፁ። የክልሉ ጤና ቢሮ ለደሴ አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በ 175 ሚሊዮን ብር ወጪ የኤም. አር. አይ. ህክምና ማሽን ድጋፍ ያደረገ ሲሆን፤ በሆስፒታሉ በ150 ሚሊዮን ብር የተገነባው ባለ አራት ወለል ሕክምና መስጫም ሕንፃ ተመርቋል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር)፤ የክልሉን ሰላም በመጠበቅ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሰፋፊ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን ገልፀዋል። በተለይም የጤና፣ የትምህርትና የሌሎችንም ማህበራዊ ተቋማት ደረጃን በማሻሻልና በማጠናከር የተሻለ አገልግሎት እንዲሰጡ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በደሴ አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ተገንብቶ ዛሬ የተመረቀው ዘመናዊ ህንጻ እና ድጋፍ የተደረገው ዘመናዊ ማሽን የዚሁ አካል መሆኑን ጠቁመው፤ ህብረተሰቡ የተሻለ እና ጥራት ያለው አገልግሎት ማግኘት እንዲችል እድል የሚፈጥር ነው ብለዋል። የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱልከሪም መንግሥቱ በበኩላቸው፤ በክልሉ የጤና ተቋማትን በቴክኖሎጂ በማደራጅትና ደረጃቸውን በማሻሻል ጥራት ያለው ህክምና እንዲሰጡ እየተደረገ ነው ብለዋል። በዚህም በሆስፒታሉ የማስፋፊያ ግንባታ ከማድረግ ባለፈ ዘመናዊ ግብዓትም እየተሟላ ሲሆን ለሆስፒታሉ የኤም. አር. አይ. ማሽን ድጋፍ ተደርጓል ብለዋል። ማሽኑ ለረጅም ጊዜ ሲጠየቅ እንደነበረ ጠቁመው፣ ከፍተኛ የቀዶ ህክምና ለመስጠት ሲፈለግ የውስጥ በሽታዎችን ለመለየት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። የደሴ አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ሥራ አስኪያጅ ዶክተር ሀይማኖት አየለ በበኩላቸው፣ ሆስፒታሉን ዲጂታላይዝ ከማድረግ ባለፈ በቴክኖሎጂ የታገዘ ግብዓት በማሟላት ጥራት ያለው ህክምና እንዲሰጥ እየተደረገ ነው ብለዋል። ሆስፒታሉ ከአማራ ክልል በተጨማሪ ከአፋር እና ከትግራይ ክልሎች ለሚመጡ ዜጎችም ጭምር አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ነው የተናገሩት። ዛሬ የተመረቀው ህንጻም አገልግሎቱን የበለጠ በማቀላጠፍና በማሻሻል ጥራት ያለው ህክምና ለመስጠት እንደሚያግዝም ነው የተናገሩት።   በፕሮግራሙ የክልል፣ የወሎ ዩኒቨርሲቲ፣ የደቡብ ወሎ ዞንና የደሴ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች፣ የሐይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።  
በጋምቤላ ክልል ፍትሐዊና ጥራቱን የጠበቀ የጤና አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ የጤና መድህን ተጠቃሚነት ይበልጥ ይጠናከራል
Feb 25, 2026 120
ጋምቤላ፤ የካቲት 18/2018 (ኢዜአ)፦ በክልሉ የጤና መድህን ስርዓቱን በማጠናከር ፍትሐዊና ጥራቱን የጠበቀ የጤና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። የክልሉ ጤና ቢሮ የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን ምክር ቤት ክልላዊ የንቅናቄ መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ አካሂዷል።   የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ አለሚቱ ኡሞድ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የጤና መድህን አገልግሎቱ ዜጎች ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት እንዲያገኙ የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ። በተለይም በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች በአነስተኛ ወጪ የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙና ጤናቸው እንዲጠበቅ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ የጤና መድህን አገልግሎቱን ለማጠናከርና የዜጎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመረው ጥረት ይበልጥ ተጠናከሮ የሚቀጥል መሆኑንም ነው ያስታወቁት። የጤና መድህን አገልግሎቱን በክልሉ በሁሉም አካባቢዎች ተደራሽ ለማድረግ እየተከናወነ ለሚገኘው ስራ ስኬታማነት የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ነው ያረጋገጡት።   የኢትዮጵያ ጤና መድህን አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ወይዘሮ ያምሮት አንዱዓለም በበኩላቸው የጤና መድህን አገልግሎት ጤናማ ማህበረሰብን ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ የሚገኝ ነው ብለዋል። እንደ ሀገር አገልግሎቱ ከተጀመረ ወዲህ ከ63 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን ካልታሰበ የህክምና ወጭ በመታደግ ፍትሃዊ የጤና አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል። እንዲሁም ከፍለው መታከም ለማይችሉ 17 ሚሊዮን ለሚሆኑ ዜጎች ነፃ የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግ መቻሉንም ነው ያስረዱት። በጋምቤላ ክልልም ለዜጎች የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት አበረታች መሆናቸውን ገልጸዋል። የንቅናቄ መድረኩ ዋና አላማም የአባላት ምዝገባና እድሳትን በማጠናከር ለዜጎች የሚሰጠውን አገልግሎት ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ ያለመ መሆኑንም ምክትል ዋና ዳይሬክተሯ ተናግረዋል።   የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አቤል አሰፋ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት የጤና መድህን አገልግሎት በክልሉ ከሚገኙ 14 ወረዳዎች ውስጥ በ13ቱ ተደራሽ ለማድረግ ተችሏል።  
የዓድዋ ድል ከቀደሙት አያቶቻችን የተቀበልነው የሀገር ፍቅር ምልክትና የጀግንነት ስንቅ ነው
Feb 25, 2026 103
ሐረር፤የካቲት 18/2018 (ኢዜአ) ፡-የዓድዋ ድል ከቀደሙት አያቶቻችን የተቀበልነው የሀገር ፍቅር ምልክትና የጀግንነት ስንቅ ነው ሲሉ የምስራቅ እዝ የሰራዊት አባላት ገለጹ። በሀገር መከላከያ ሰራዊት የምስራቅ እዝ አባላት 130ኛውን የዓድዋ ድል በዓል "ከአኩሪ ታሪክ ወደ ብሩህ አድማስ" በሚል መሪ ሃሳብ በሐረር ከተማ ራስ እምሩ መሰብሰቢያ አዳራሽ በፓናል ውይይት አክብረዋል።   በመድረኩ ላይ የተሳተፉ የሰራዊቱ አመራሮችና አባላት የዓድዋን በአል ስናከብር የኢትዮጵያን ክብርና ሉአላዊነት በጀግንነት ለመጠበቅ ዳግም ቃል በመግባት ነው ብለዋል። ከእዙ አመራሮች መካከል ኮለኔል መላኩ ዘገዬ፤ የዓድዋ ድል ኢትዮጵያዊያን በጋራ ቆመው የሀገራቸውን ክብርና ሉአላዊነት ያስከበሩበት የመላ ጥቁር ህዝቦች የአሸናፊነት ምልክት መሆኑን ገልጸዋል።   ዓድዋ የአሁኑ ትውልድ ከቀደሙት የሀገር ፍቅርን፣ ጀግንነትንና ህብረ ብሄራዊ አንድነትን የሚማርበት ስለመሆኑ አንስተው፤ የዓድዋ ድል ከአያቶቻችን የተቀበልነው የሀገር ፍቅር ምልክትና የጀግንነት ስንቅ ነው ሲሉ ተናግረዋል። የዓድዋ ድልን የተረከበው ትውልድ የህዳሴ ግድብን በመገንባት የልማት ድል አድራጊነቱን ማሳየቱን ገልጸው፤ የኢትዮጵያን ሰላም ለማናጋትና ልማቷን ለማደናቀፍ የሚጥሩ አካላትን ሰራዊታችን አይታገስም ሲሉ አረጋግጠዋል።   ሌሎች የእዙ አመራሮች ሻምበል ሂሩት እምዩ እና ሻለቃ ሀሮን ገርቢ፤ በአድዋ የተመዘገበውን የአሸናፊነት ደማቅ የታሪክ አሻራ በጀግንነት እንዲቀጥል ማድረግ የዚህ ትውልድ አደራና ሃላፊነት መሆኑን ገልጸዋል። የመላ ጥቁር ህዝቦች የአሸናፊነት ቀንዲል የሆነውን የዓድዋ ድል በመሰነቅ ለኢትዮጵያ ሰላም እድገትና ማንሰራራት በፅናት መቆማቸውን አረጋግጠዋል።   ሌላኛው የመድረኩ ተሳታፊ ሌተናል ኮለኔል መስፍን አባተ፤ የዓድዋ ድል አያቶቻችን በቅኝ ግዛት ስር እንዳንወድቅ መስዋዕት በመክፈል ያስረከቡን ታላቅ አደራ በመሆኑ ሁሌም እንዘክረዋለን ብለዋል።   የጀግኖች አርበኞች ተተኪ ትውልዶች ሆነን ለአገር ሉዓላዊነት መከበር መስዋእትነት አየከፈልን ኢትዮጵያ ታፍራና ተከብራ እንድትኖር የሚጠበቅብንን እንወጣለን ሲሉም አረጋግጠዋል። የፓናል ውይይቱን የመሩት ኮሎኔል ደምሌ አማረ፤ የዓድዋ ድል የይቻላልና የአይበገሬነት መንፈስን በማህበረሰቡና በሰራዊቱ እንዲሰፍን አድርጓል።   ሰራዊቱም ከቀደምቶች በወረሰው ጀግንነት ሀገሩን በሁሉ መስክ ሳያስደፍር እንድትቀጥል ማድረጉን ገልጸው በዚህም አሁን የተመዘገበውን የልማት ጉዞ ማስቀጠል እንደሚገባም አስገንዝበዋል።  
በዓድዋ ድል ጀግኖች አባቶች ያሳዩትን ጥንካሬና አንድነት ወጣቱ ትውልድ በልማት ሊደግመው ይገባል
Feb 25, 2026 98
የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦በዓድዋ ድል ሁሉም ኢትዮጵያዊያን ያሳዩትን የሀገር ፍቅርና ጠንካራ የአንድነት ስሜት ወጣቱ ትውልድ ሊያስቀጥለውና በልማቱ ሊደግመው እንደሚገባ በሲዳማ ክልል የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር አስታወቀ፡፡ 130 ኛው የዓድዋ ድል በዓል መታሰቢያ በመጪው ሰኞ የካቲት 23 ቀን 2018 ዓ.ም በተለያዩ ዝግጅቶች ይከበራል፡፡ የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን በጋራ ቆመው የሀገር ክብርና ሉዓላዊነት ያስጠበቁበት የመላ ጥቁር ህዝቦች የአሸናፊነት ምልክት ነው በሲዳማ ክልል የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ሊቀመንበር አቶ የኋላእሸት ቸርነት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የዓድዋ ድል የመላው ኢትዮጵያውያን ጥልቅ የሀገር ፍቅር ስሜትና አንድነት የተገለፀበት ነው፡፡ ወጣቱ ትውልድም በዓድዋ ድል የታየውን የሀገር ፍቅር፣ አንድነትና አይበገሬነት ሊያስቀጥለውና በልማቱም ሊደግመው እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ የዓድዋ ድል ለኢትዮጵያውያን ኩራት፣ ለመላው ጥቁር ህዝቦች ደግሞ የነጻነት ጮራ የፈነጠቀበት በመሆኑ መታሰቢያውን ስናከብር የቀደሙ አባቶችን አርዓያነት ያለው ተግባር በማስቀጠል መሆን አለበት ብለዋል፡፡ የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን በሀገር ጉዳይ ልዩነት እንደሌላቸውና በሉዓላዊነታቸው እንደማይደራደሩ ያሳዩበት ጭምር መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ሀገር የምትገነባው በትውልድ ቅብብሎሽ መሆኑን የገለጹት አቶ የኋላእሸት የትናንት አባቶች ያስረከቡንን ነጻ ሀገር በልማት ማሳደግና ቀዳሚ ማድረግ ይገባል ብለዋል፡፡ በዚህም በኢኮኖሚ የዳበረች ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመገንባት መንግስት የጀመራቸውን ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች በመደገፍ የልማት አርበኛ መሆን ይገባል ብለዋል፡፡ ማህበራቸው የዓድዋ ድል መታሰቢያ ቀንን በማስመልከት በተለያዩ ትምህርት ቤቶች በመገኘት ትውልዱን ማስተማር መጀመሩን የገለጹት ደግሞ የማህበሩ አባል የሆኑት ወይዘሮ ገነት ለማ ናቸው፡፡   የዓድዋ ድል ጀግኖች አባቶች ለሃገር ሉዓላዊነት የከፈሉት መስዋእትነት በደማቅ ቀለም የተፃፈበት መሆኑን ትውልድ በተገቢው ሊረዳውና ሊያስቀጥለው እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡ ድሉ በመላ ኢትዮጵያውያን አንድነትና ትብብር የተገኘ መሆኑን ጠቅሰው በዓሉን ስናከብር ትምህርት በመውሰድ መሆን አለበት ብለዋል፡፡ የዓድዋ ድል ለትውልዱ ጀግንነትን፣ አንድነትንና አብሮነትን ያስተማረ የጥቁር ህዝቦች ድል ሲሆን የሃገር ፍቅርና የሰንደቅ ዓላማ ክብር የተገለፀበት የጋራ ታሪክ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን በጋራ ቆመው የሀገር ክብርና ሉዓላዊነት ያስጠበቁበት የመላ ጥቁር ህዝቦች የአሸናፊነት ምልክት ነው
Feb 25, 2026 97
አዲስ አበባ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦ የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን በጋራ ቆመው የሀገር ክብርና ሉዓላዊነት ያስጠበቁበት የመላ ጥቁር ህዝቦች የአሸናፊነት ምልክት መሆኑን የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ። 130ኛውን የዓድዋ ድል በዓል ''ከአኩሪ ታሪክ ወደ ብሩህ አድማስ'' በሚል መሪ ሐሳብ የፊታችን የካቲት 23/2018 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጃ ይከበራል፡፡ የዓድዋ ድል የጥቁር ህዝቦች የነጻነት ፋና ወጊ እና የኢትዮጵያውያን የአንድነት ተምሳሌት ሲሆን ይህ ድል ዛሬም ድረስ ለሀገራዊ ልማትና ለሉዓላዊነት መከበር እንደ ትልቅ ስንቅ እየተጠቀሰ ይገኛል። 130ኛውን የዓድዋ ድል "ከአኩሪ ታሪክ ወደ ብሩህ አድማስ" በሚል መሪ ሀሳብ ለማክበር ዝግጅት ተጠናቋል ድሉ የኢትዮጵያ ህዝቦች ከግል ፍላጎት የሀገርን ክብርና ሉዓላዊነት ማስቀደምን ያስተማረ መሆኑን ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ ምሁራን ይናገራሉ። በሀረማያ ዩኒቨርሲቲ የሰላም እና ልማት ተመራማሪ የሆኑት ጌጤ ነገሪ፣ ጀግኖች አባቶቻችን የውስጥ ልዩነቶቻቸውን ወደ ጎን በመተው በአንድነት ጸንተው ሀገራቸውን ከወራሪ ነጻ ማድረግ ችለዋል ብለዋል።   በወቅቱ የሀገራችን ህዝቦች በሁሉም አቅጣጫ በጋራ ቆመው ባሳዩት ጥንካሬ ዘመናዊ የጦር መሳሪያ ያነገበውን ወራሪ ኃይል ማሸነፍ እንደሚቻል ያሳዩበት ትልቅ ድል ነው ብለዋል። ትውልዱ አሁን ላይ ተባብሮና ተስማምቶ በመስራት ታላቁን የህዳሴ ግድብና ሌሎች አንጸባራቂ የልማት ድሎችን ማስመዝገብ እንደቻለ ሁሉ አንድነቱን አጠናክሮ የተጀመሩ ታላላቅ ፕሮጀክቶችን ከዳር ማድረስ እንዳለበት መክረዋል። ይህ ብቻ ሳይሆን የዛሬው ትውልድ ከዓድዋ ጀግኖች በወረሰው ወኔ ብሔራዊ ጥቅምን ማስጠበቅ እና የባህር በር የባለቤትነት መብትን ለማስመለስ መትጋት አለበት ብለዋል። በሀረማያ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ ምሁር ታሪኩ ራጋ ፤ ዓድዋ አባቶቻችን በአንድነት ሆነው ውድ ህይወታቸውን ከፍለው ኢትዮጵያን ያስከበሩበት የድል ታሪክ መሆኑን አስረድተዋል።   የዛሬው ትውልድም ታላላቅ ድሎችን እያስመዘገበ መሆኑን ጠቅሰው ከነዚህ መካከል የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ተጠቃሽ ነው ብለዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ ምሁሩ መብራቴ ጊርግሶ፤ የዓድዋ ድል የሀገር ባለቤትነት ስሜት መገለጫ እና የኢትዮጵያዊነት ጽናት መሰረት መሆኑን ተናግረዋል።   የዓድዋ ድል ጥቁር ህዝቦች በጋራ በመሆን ማንኛውንም ነገር ማሸነፍ እንደሚችሉ ማሳያ መሆኑን አንስተው አሁን የውስጥ ችግሮቻችንን በንግግር በመፍታት ለብሔራዊ ጥቅም መቆም ይጠበቅብናል ሲሉም ገልጸዋል። በታሪክ እና ህዝብ አስተዳደር ዙሪያ የተለያዩ ጥናቶችን የሚያካሄዱት ብርሃኑ ሌንጅሶ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የዓድዋ ድል የአንድነትና ጥንካሬ ውጤት መሆኑን አንስተው በዚህ ዘመንም ድሉ በህዳሴ ግድብ የተደገመ መሆኑን ገልጸዋል።   ድሉ አፍሪካኒዝምን በማጠናከር አለም በማንነት ላይ ያላትን የተንሸዋረረ እይታ መለወጥ የተቻለበትና ህዝቡ ጥቃቅን ልዩነቶችን ወደ ጎን በመተው ባሉት የጋራ ጉዳዮች ላይ ጠንክሮ ከሰራ የማያሳካው ነገር እንደሌለ የሚያሳይ ነው ብለዋል። የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን ለሀገራቸው በጋራ ቆመው ክብርና ሉዓላዊነቷን ያስጠበቁበት የመላ ጥቁር ህዝቦች የአሸናፊነት ምልክት መሆኑን አስረድተዋል። ትውልዱ እንደ አባቶቹ ብሔራዊ ጥቅሙን ለማስከበር የባህር በር ባለቤትነት ላይ አንድነቱን አጠናክሮ ሊቆም ይገባል ብለዋል።
ኢትዮጵያን የሕክምና ቱሪዝም መዳረሻ የማድረግ ተግባር ይጠናከራል
Feb 25, 2026 78
ደሴ ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያን የሕክምና ቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የጤና ሚኒስቴር ገለፀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በቅርቡ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ ከአፍሪካም ሆነ ከሌሎች አካባቢዎች ለህክምና ወደ ኢትዮጵያ የመምጣት ዝንባሌ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተለመደ በመሆኑ እድሉን ለመጠቀም የተጠናከረ ስራ መስራት እንደሚገባ መግለጻቸው ይታወሳል። ይህንኑ በተመለከተም የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጄ ዱጉማ እንደገለጹት፤ የጤና ተቋማትን አቅም በማሳደግ፣ በቴክኖሎጂና በሰው ኃይል በማጠናከርና ግብዓትን በማሟላት ኢትዮጵያን የሕክምና ቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ እየተሰራ ነው። ኢትዮጵያ በሕብረተሰብ ጤና አደጋዎች ክትትልና ቁጥጥር ስኬታማ ተግባር አከናውናለች ለዚህም ከአዲስ አበባ ከተማ በተጨማሪ በሌሎች የክልል ከተሞችም ግዙፍ ሆስፒታሎች እየተገነቡ ሲሆን የውስጥ ግብዓታቸው እንዲሟላ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይ አምስት ዓመታት ዘርፉን በማሳደግ ኢትዮጵያን የህክምን ቱሪዝም ማእከል ለማድረግ ግብ ተይዞ እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቁመው የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ነው የተናገሩት። አሁን ላይ በዓይን፣ በጥርስ፣ በአንጎል፣ በመካንነትና በሌሎች የሕክምና ዘርፎች ላይ አፍሪካውያን ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ህክምና እያገኙ መሆኑን ጠቁመው በቀጣይ ዘርፉን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር እንደሚሰራ ነው ያረጋገጡት። ለዚህም ለአቅም ግንባታ ስራ ትኩረት በመስጠት የሕክምና ባለሙያዎች ወደ ውጭ ሔደው በስፔሻሊስትና ሰብ ስፔሻሊስት ስልጠና እንዲወስዱ እየተደረገ መሆኑን ገልፀዋል። በተመረጡ ሆስፒታሎችም ዘመኑ የደረሰባቸው ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመው አገልግሎት እንዲሰጡ ዘመናዊ የሕክምና ግብዓት እንዲሟላላቸው እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል። መሰረታዊ የሕክምና መሳሪያዎችንና መድኃኒቶችን በሀገር ውስጥ ለማምረት በተደረገው ጥረትም 40 በመቶ የሚሆነውን ማሳካት መቻሉን ተናግረዋል። እስከ ቀጣዩ ዓመት የሀገር ውስጥ ምርቱን ወደ 60 በመቶ ከፍ በማድረግ ለዘርፉ የሚወጣውን የውጭ ምንዛሬ ለማዳን ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። ዜጎች ወደ ውጭ ለሕክምና እንዳይሄዱና እንዳይንገላቱ ከማድረግ ባለፈ አፍሪካውያን ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ጥራት ያለው ህክምና እንዲያገኙ እየተሰራ ነው ብለዋል። በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን የኩታበርና ሱሉላ ጤና ጣቢያዎች በአጋር አካላት ድጋፍ የደረጃ ማሻሻያ ከተደረገላቸው በኋላ ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸው ይታወሳል።
ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ግጭቶችን በመፍታትና ፍትህን በማስፈን ረገድ ውጤታማ ሆነዋል
Feb 25, 2026 100
ጊምቢ ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ወለጋ ዞን ወደ ስራ የገቡ ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ግጭቶችን በመፍታትና ፍትህን በማስፈን ረገድ ውጤታማ መሆናቸውን ተገልጋዮች ገለጹ። በኦሮሚያ ክልል መነሻውን የገዳ ሥርዓት በማድረግ ግጭቶችን እና አለመግባባቶችን ለመፍታት ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ህጋዊ መሰረት ኖሯቸው እየሰሩ ይገኛሉ። የምዕራብ ወለጋ ዞን ባህላዊ ፍርድ ቤቶች በተለያዩ ምክንያቶች የሚነሱ ግጭቶችና አለመግባባቶችን በእርቅ በመፍታት፣ እውነተኛ ፍትህ እያገኙ መሆኑን ነዋሪዎች ገለጸዋል። ባህላዊ ፍርድ ቤቶች የመደበኛ ፍርድ ቤቶችን የስራ ጫና በመቀነስና ማህበረሰባዊ እሴትን በማጠናከር በኩል ውጤት እያስገኙ ነው   ነዋሪዎቹ ቀደም ሲል በመደበኛ ፍርድ ቤቶች ጉዳያቸውን ለማስፈጸም ለተለያዩ እንግልቶችና ወጪዎች ይዳረጉ እንደነበርም አስታውሰዋል። ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አለመግባባቶችን በአጭር ጊዜ በእርቅ በመፍታት፣ ፍትህ እንዲሰፍን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑ ተመልክቷል።   በኢናንጎ 02 ቀበሌ በባህላዊ ፍርድ ቤት የቤተሰባቸውን የንብረት ውርስ ለማስከበር የመጡት ወይዘሮ ጣይቱ ኩመራ፤ ጉዳያቸውን ተቀባይነት ባላቸው የሀገር ሽማግሌዎች አማካኝነት በጥቂት ቀናት ውስጥ ማስፈጸማቸውን ተናግረዋል። ህብረተሰቡ ባህልና ወጉን ጠብቆ ችግሮችን በእርቅ እንዲፈታ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው፤ ሁሉም አካላት ባህላዊ ፍርድ ቤቶች እንዲጠናከሩ የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። ሌላው የላሎ አሳቢ ወረዳ ነዋሪ አቶ ጉታታ ዲቢሳ በበኩላቸው፤ ባህላዊ ፍርድ ቤቶች የማህበረሰቡን እሴት ተከትለው የሚሰሩ በመሆናቸው የሀሰት ምስክርነትን በማስቀረት እውነተኛ ፍትህ እንዲሰፍን እያገዙ መሆኑን ገልጸዋል።   በመደበኛ ፍርድ ቤቶች ጉዳይ ለማስፈጸም የነበረውን እንግልት በመቀነስ፣ በሀገር ሽማግሌዎችና በአባገዳዎች አማካኝነት ፍትህ ሳይጓደል መፍትሄ ማግኘት መቻሉን አብራርተዋል። የቡና መሬት የወሰን ችግር አጋጥሟቸው ወደ ባህላዊ ፍርድ ቤት የመጡት አቶ ጫላ ቀነኣ፤ ጉዳያቸው በገዳ ሥርዓት መሠረት ውሳኔ አግኝቶ በእርቅ እንዲጠናቀቅ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።   የዞኑ ባህልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ተወካይ አቶ ምስጋኑ ደገፋ እንደገለጹት፤ ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ህብረተሰቡ በአቅራቢያው ፍትህ እንዲያገኝ እያደረጉ ነው። በአሁኑ ወቅትም በዞኑ 481 ባህላዊ ፍርድ ቤቶች ተቋቁመው ስራ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በዞኑ ማህበረሰቡ ባህልና እሴቱን ጠብቆ አለመግባባቶችን በእርቅ እንዲፈታ ማስቻል እንዲሁም በህዝቡ ዘንድ የሚስተዋሉ ውስብስብ ችግሮችን በማስቀረት ረገድ ትርጉም ያለው ስራ እየተሰራ መሆኑንም አቶ ምስጋኑ አክለው ገልጸዋል።
መገናኛ ብዙሃን በነፃነት እንዲሰሩ የሚያስችል አውድ ለመፍጠር በርካታ ስራዎች ተሰርተዋል 
Feb 24, 2026 95
አዲስ አበባ፤ የካቲት 17/2018(ኢዜአ)፦ መገናኛ ብዙሃን በነፃነት እንዲሰሩ የሚያስችል አውድ ለመፍጠር በርካታ ስራዎች መሰራታቸውን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ፡፡ አቶ አደም ፋራህ በፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ተገኝተው የተቋሙን የሥራ እንቅስቃሴና ያከናወናቸውን የማሻሻያ ተግባራት ጎብኝተዋል፡፡   በጉብኝታቸውም ምቹ የስራ ከባቢን ከመፍጠርና ተወዳዳሪነትን ከማላቅ አንጻር በርካታ ስራዎች እንደተሰሩ መመልከታቸውንና ይህም ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽንን ይበልጥ ጠንካራና ተወዳዳሪ እንዲሆን ያስችለዋል ብለዋል፡፡ ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን በኢትዮጵያ የሚዲያ ታሪክ ጉልህ አሻራ ያሳረፈ ተቋም መሆኑን አንስተው በአሁኑ ወቅት ለዘመኑ የመገናኛ ብዙሃን ውድድር የሚያግዙ ስራዎች መሰራታቸውን መጥቀሳቸውንም እንዲሁ፡፡ ተቋሙ ዘመናዊነትን ከህዝብ አመኔታ ጋር ያቀናጀ በመሆኑ ተልዕኮውን በተሳለጠ መንገድ እንዲወጣ የሚያስችለው ቁመና ላይ እንዲገኝ አግዞታል ነው ያሉት፡፡   ከለውጡ ወዲህ መገናኛ ብዙሃንን በተለያዩ ተቋማት የተከናወኑ የማሻሻያ ተግባራት አካል በማድረግ በርካታ ሥራዎች መሰራታቸውን ነው አቶ አደም ፋራህ የገለጹት፡፡ ከዚህ ቀደም መገናኛ ብዙሃን በነፃነት እንዳይሰሩ የሚገድቡ የህግ ማዕቀፎችን በማሻሻል በነፃነት እንዲሰሩ የሚያስችላቸውን አውድ ለመፍጠር ሲሰራ መቆየቱንም ተናግረዋል፡፡ ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽንም ከለውጡ ወዲህ የተገኙ የመገናኛ ብዙሃን ነፃነትን በአግባቡ እየተጠቀመ ይገኛል ሲሉ መናገራቸውንም ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን በዘገባው አስነብቧል፡፡
የኢትዮጵያ ፖሊስ ሰራዊት በአፍሪካ የነጻነት ትግል ታሪክና ለዓለም ሰላም ዘብ በመቆም ግንባር ቀደም ሚና አለው
Feb 24, 2026 99
አዲስ አበባ፤ የካቲት 17/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ፖሊስ ሰራዊት በአፍሪካ የነጻነት ትግል ታሪክና ለዓለም ሰላም ዘብ በመቆም ግንባር ቀደም ሚና እንዳለው የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አዛዥ ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ገለጹ፡፡ የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንትና የጸረ አፓርታይድ ታጋይ ኔልሰን ማንዴላ በሰለጠኑበት ኮልፌ ፌዴራል ፖሊስ ፈጥኖ ደራሽ ግቢ የተሰየመው የመታሰቢያ ሙዚየም ተመርቋል። በምረቃ መርሃ-ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አዛዥ ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል፣ በኢትዮጵያ የደቡብ አፍሪካ አምባሳደር ኖንሴባ ሎሲ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።   የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አዛዥ ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ የዘመናዊ ፖሊስ ምስረታ 117 ዓመታትን ያስቆጠረ ከአፍሪካ ቀዳሚው ተቋም ነው። የኢትዮጵያ ፖሊስ ለአፍሪካ የነፃነት ትግል የጎላ አበርክቶ እንዳለው ገልጸው፤ የዓለም ጥቁር ህዝቦች የነፃነት አባት የሆኑትን የቀድሞው የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ኔልሰን ማንዴላ አሰልጥኗል ብለዋል። ኔልሰን ማንዴላ የፀረ አፓርታይድ ትግልን ለመቀላቀል እ.ኤ.አ በ1962 በኢትዮጵያ ለወራት ስልጠና መውሰዳቸውን ገልጸዋል። ኔልሰን ማንዴላ በኢትዮጵያ ለመሰልጠን የመረጡት ኢትዮጵያ ቅኝ ያልተገዛችና የዓለም ጥቁር ህዝቦች ምልክት በመሆኗ ነው ብለዋል። ኔልሰን ማንዴላ በኢትዮጵያውያን የፖሊስ አባላትና መኮንኖች መሰልጠናቸውን ጠቅሰው፤ ብርጋዴር ጄኔራል ታደሰ ብሩ፣ ኮሎኔል ፈቃዱ ዋኬኔ፣ መቶ አለቃ ፈቃዱ ወንድም ከአሰልጣኞች መካከል መሆናቸውን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ ፖሊስ እውቀትና ልምዱን በማካፈል ለደቡብ አፍሪካ የነፃነት ትግል ገንቢ ሚና ተወጥቷል ብለዋል።   ኢትዮጵያ በደቡብ አፍሪካ ነጻነት ታሪክ ቀረጻ ላይ ተሳትፎ እንዳላት ያነሱት ኮሚሽነር ጀነራሉ፤ ይሄውም የኢትዮጵያ ፖሊስ ተቋም የላቀ ሙያዊ ስነ-ምግባሩንና ሀገራዊ ሀላፊነቱን የተወጣበትን መንገድ እንደሚያሳይ ገልጸዋል፡፡ የኔልሰን ማንዴላ መታሰቢያ ሙዚየም በኢትዮጵያና ደቡብ አፍሪካ መካከል ያለውን ወዳጅነት የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ሰላምና ደህንነት የምታበረክተው አስተዋፅኦ ለዓለም ሰላም መረጋገጥ ያላትን ቁርጠኝነት ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም