ቀጥታ፡
ማህበራዊ
ወጣቶች ዓመቱን ሙሉ በሚያከናውኗቸው የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች ማኅበራዊ ኃላፊነታቸውን እየተወጡ ይገኛሉ
Jul 11, 2026 343
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ ወጣቶች በክረምትና በበጋ የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች በመሳተፍ ማኅበራዊ ኃላፊነታቸውን እየተወጡ እንደሚገኙ በብልፅግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ የወጣቶች ክንፍ የጽሕፈት ቤት ኃላፊ መለሰ አባተ ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ብልፅግና ፓርቲ ወጣቶች ክንፍ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎትን በማስመልከት የደም-ልገሳ መርሐግብር አከናውነዋል፡፡ አባላቱ ይህንን አርዓያነት ያለው ተግባር በቀጣይም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በብልፅግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ወጣቶች ክንፍ የጽሕፈት ቤት ኃላፊ መለሰ አባተ እንደገለጹት፤ ወጣቶቹ ማኅበራዊ ኃላፊነታቸውን ለመወጣት ዓመቱን ሙሉ በተለያዩ የልማትና የበጎ ፈቃድ ሥራዎች ላይ ንቁ ተሳትፎ እያደረጉ ይገኛሉ ብለዋል። በዚሁ መሠረት የክረምት የበጎ ፈቃድ መርሐ ግብሩ አካል የሆነ የደም ልገሳ መርሐ ግብር በዛሬው ዕለት የተከናወነ ሲሆን፣ ከ1 ሺህ በላይ ወጣቶች ደም በመለገስ አርዓያነታቸውን ማሳየታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ወጣቶቹ በማኅበረሰብ አገልግሎት ተሳትፏቸው የሚያበረክቱት አስተዋጽኦ ለሀገራዊ አብሮነትና ለዜግነት ግዴታ መወጣት ትልቅ ሚና ያለው በመሆኑ፣ ተሳትፏቸውን በቀጣይም በላቀ ሁኔታ እንደሚያጠናክሩት አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ብልፅግና ፓርቲ የወጣቶች ክንፍ አባላት፣ በደም እጥረት ምክንያት የሚከሰቱ ጉዳቶችን ለመቀነስ ትኩረት አድርገው በተለያዩ የበጎ ፈቃድ ሥራዎች ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ። በዛሬው ዕለት በተከናወነው የደም ልገሳ መርሐ ግብር ላይ የተሳተፉ ወጣቶች እንደገለጹት፤ ደም መለገስ የሰው ልጅን ሕይወት የመታደግ አርዓያነት ያለው ተግባር ነው ብለዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ አስተያየታቸውን ከሰጡት ወጣቶች መካካል ብርቱካን ገብሬ እንዳለችው ደም መለገስ መስጠት ከባድ ኃላፊነትና ሰብአዊ ግዴታ መሆኑን ተናግራለች፡፡ ወጣት ጉዲና ስሜ ደም መለገስ የዘወትር ተግባሩ እንደሆነ ገልጾ፣ ደም ከመለገስ ባለፈም በሌሎች የበጎ ፈቃድ ሥራዎች ተሳትፎውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጿል። በደም ልገሳ መርሐ ግብር ላይ ለሰባተኛ ጊዜ መሳተፏን የገለጸችው አዲስ ሙሉጌታ በበኩሏ በጎ ፈቃደኝነት የህሊና እረፍት የሚሰጥ ተግባር መሆኑን ጠቅሳለች፡፡ ወጣቶች እያከናወኑት የሚገኘው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ የዜግነት ግዴታቸውን ከመወጣት ባሻገር ለማኅበረሰቡ ደኅንነት ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው።
የህፃናት መብትና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚከናወኑ  ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ  
Jul 11, 2026 634
ሀረር፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የህፃናት መብትና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ሁሉን አቀፍ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) ገለጹ። ‘የተጠበቁ ህጻናት ለበለፀገ ትውልድ’’ በሚል መሪ ሃሳብ የአፍሪካ ህፃናት ቀን ማጠቃለያ ፕሮግራም በሐረር ከተማ ተካሂዷል።   በስነ ስርአቱ ላይ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር)፣የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር፣ ሚኒስትር ዴዔታዎች፣ የህጻናት ፓርላማ አፈ ጉባዔዎች፣ ታዳጊ ህፃናትና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) በወቅቱ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት፤ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በመሆን ለነገ ሀገር ተረካቢ ህጻናት አስፈላጊው መሰረተ ልማቶች የማሟላት ስራ እየተከናወነ ነው።   በተለይም ውብ፣ ምቹና ጽዱ የመዝናኛ እንዲሁም የህጻናት ማቆያና መንከባከቢያ ማዕከላትንና የመጫወቻ ስፍራዎች የመገንባትና የማስፋፋት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከዚሁ ጎን ለጎን የህጻናት ድጋፍና እንክብካቤ፣ በተለያዩ ዘርፎች ተሷትፏቸውን የማጎልበት እንዲሁም በጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ተጎጂ እንዳይሆኑ የመጠበቅ፣ ከጥቃት የመከላከልና ሌሎች በርካታ ስራዎችም ስለመከናወናቸው አመልክተዋል። ከማህበረሰቡና ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የነገ ሀገር ተረካቢ የሆኑ ህፃናትን መብትና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ሁሉን አቀፍ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል ። የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር በበኩላቸው፤ በክልሉ በከተማም ሆነ በገጠር ያሉ ህጻናት መብት፣ ደህንነትና ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ የልማት ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል።   የህጻናት ሁለንተናዊ እድገት ስኬታማ የሚሆነው በመንግስት ጥረት ብቻ አለመሆኑን ጠቁመው በክልሉ በገጠርና በከተማ ያሉ ህጻናት እኩል ተጠቃሚና ተደራሽነትን ለማጎልበት የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ተሳትፎን ማጎልበት እንደሚገባ አመልክተዋል። በሀገሪቱ የህጻናትን መብት በማስከበር ረገድ መሻሻሎች እየታዩ መሆኑን የተናገረችው ደግሞ የሀገር አቀፍ የህጻናት ፓርላማ ዋና አፈ ጉባዔ ህፃን ብሌን ድልአርጋቸው ናት።   የህጻናትን መብትና ደህንነት የማስጠበቅና ተጠቃሚነትን ከማጎልበት አንጻር መንግስትና ባለድርሻ አካላት እያከናወኑ የሚገኘው ስራ ተጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቃለች።
በትምህርት ዘርፍ ብቁ፣ ተወዳዳሪና በሥነ-ምግባር የታነጸ ሀገር ተረካቢ ትውልድ ለማፍራት ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jul 11, 2026 565
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ በትምህርት ዘርፍ ብቁ፣ ተወዳዳሪና በሥነ-ምግባር የታነጸ ሀገር ተረካቢ ትውልድ ለማፍራት ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ አየለች እሸቴ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ በመገኘት፣ የትምህርት ዘርፍን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ፤ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ የተቀናጁ ተግባራት በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ለውጥ እየመጣ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የትምህርት መሠረትን ከታች ጀምሮ ለማጠናከር በትኩረት መሠራቱን ጠቁመው፤ ባለፉት ሰባት ዓመታት ውስጥ ብቻ 35 ሺህ የሚሆኑ ቅድመ-መደበኛ ትምህርት ቤቶች መገንባታቸውን ተናግረዋል። ይህ የመዋዕለ ሕፃናት ግንባታ ቁጥር እጅግ ከፍተኛና ለዘርፉ የተሰጠውን ልዩ ትኩረት የሚያሳይ መሆኑንም አብራርተዋል።   በየደረጃው በሚገኙ የትምህርት ዘርፎች የተከናወኑ እነዚህ ዘርፈ-ብዙ ተግባራት፣ የትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ደረጃ በደረጃ በማሻሻል በኩል ከፍተኛ ሚና እያበረከቱ እንደሚገኙም አስገንዝበዋል። የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ አየለች እሸቴ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ትምህርት ትውልድ የሚቀረጽበትና ሀገር ወደ ብልጽግና ጉዞ የምትሻገርበት መሠረት መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም መንግሥት ባለፉት የለውጥ ዓመታት በአጠቃላይ በትምህርት ዘርፉ ላይ ልዩ ትኩረት በመስጠት የትምህርት ተደራሽነትንና ጥራትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ በቁርጠኝነት እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በዚህም የትምህርት ተደራሽነትን ከማስፋት ባለፈ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት እየተከናወኑ የሚገኙ በርካታ ተግባራት ውጤት እያስመዘገቡ ነው ብለዋል። የትምህርት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ በተሠራው ሥራ በርካታ የቅድመ-መደበኛ፣ የአንደኛ እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መገንባታቸውን ጠቁመዋል። በተለይም ባለፉት የለውጥ ዓመታት "ትምህርት ለትውልድ" በሚል መሪ ሀሳብ የተጀመረው ንቅናቄ ሁሉንም የማኅበረሰብ ክፍሎች ባሳተፈ መልኩ በመሰራቱ ትልቅ ውጤት እንደተመዘገበበት አረጋግጠዋል። በዚህ ንቅናቄ አማካኝነት ከ17 ሺህ በላይ አዳዲስ ትምህርት ቤቶች መገንባታቸውን፣ ከ39 ሺህ በላይ ትምህርት ቤቶች ደግሞ ዕድሳት ተደርጎላቸው የውስጥ ግብዓት እንዲሟላላቸው መደረጉን አስታውቀዋል።   መንግሥት የትምህርት ጥራት ማረጋገጥ እንዲቻል ከመሠረቱ መጀመር አለበት በሚል ለቅድመ-መደበኛ ትምህርት ልዩ ትኩረት መስጠቱን ሚኒስትር ዴኤታዋ ገልጸዋል። በዚህም መሠረት የቅድመ-አንደኛ ትምህርት ቤቶች በከተሞች ብቻ ሳይሆን በገጠርም ጭምር በከፍተኛ ሁኔታ እንዲስፋፋ መደረጉን አመልክተዋል። ለትምህርት ጥራት መረጋገጥ የሰው ኃይልን ማጠናከርና የመምህራንን አቅም መገንባት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው ከዚህ አንጻር ባለፉት ሁለት ዓመታት ብቻ ከ113 ሺህ በላይ መምህራን የአቅም ግንባታ ሥልጠና እንዲወስዱ መደረጉን ተናግረዋል። በተጨማሪም በክልሎች ከቅድመ-አንደኛ እስከ መካከለኛ ደረጃ ባሉ የትምህርት እርከኖች ላይ መምህራንን የማብቃትና አቅምን የመገንባቱ ሥራ በተጠናከረ መልኩ መቀጠሉንም ሚኒስትር ዴኤታዋ ገልጸዋል። በሥነ-ምግባር የታነጹ፣ ሥራ ፈጣሪና ሀገር ተረካቢ ዜጎችን ለማፍራት በትምህርት ዘርፉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል።
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የዜጎችን የመደጋገፍ እሴት ከፍ የሚያደርግ ነው
Jul 11, 2026 373
ሰቆጣ ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የአንድነት፣የትብብርና የመደጋገፍ እሴትን ከፍ ለማድረግ እያስቻለ መሆኑን በዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር የሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ አስታወቀ። በአስተዳደሩ የ2018 የዜጎች በጎ ፈቃድ አገልግሎት የአቅመ ደካሞችን ቤት በማደስ በሰቆጣ ከተማ በዛሬው እለት ተጀምሯል።   የመምሪያው ኃላፊ ወይዘሮ ትበርህ ታደሰ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የማህበረሰቡን ችግሮች በተደራጀ መልኩ በመፍታት የመደጋገፍ ባሕልን ለማሳደግ እያስቻለ ነው። በአስተዳደሩ በክረምቱ ወቅት በሚካሄደው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት 197 ሺህ በላይ ዜጎችን በማሳተፍ 584 ሺህ 860 የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የማድረግ ስራ መጀመሩን ገልጸዋል።   በአገልግሎቱ የአቅመ ደካማ ወገኖችን ቤቶች በአዲስ የመገንባትና የመጠገን፣ ችግኝ የመትከል፣ ደም የመለገስ ፣ የማጠናከሪያ ትምህርት በመስጠትና በሌሎች 17 የስራ ዘርፎች እንደሚከናወን አስረድተዋል። በዘንድሮው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የአንድነትና የትብብር እሴትን ይበልጥ በሚያጎለብት መልኩ ለማካሄድ በተሻለ መልኩ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በብልፅግና ፓርቲ የዋግ ኽምራ ብሄረሰብ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዳግም ባይነሳኝ በበኩላቸው፤ ከለውጡ ዓመታት ወዲህ እየተካሔዱ ባሉ የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች ስኬት እየተመዘገበበት ነው ብለዋል።   በዚህም ወጣቶችን በማስተባበር፣ በመደገፍና በማበረታታት ጥራት ያለውና ችግር ፈች የሆነ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እንዲሰጡ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። የሰቆጣ ከተማ ነዋሪ የሆነው ወጣት ጥላሁን አበበ ፤ ከጓደኞቹ ጋር በመሆን በየዓመቱ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት በመሳተፍ ወገኖቹን እያገለገለ እንደሚገኝ ነው የተናገረው።   በዘንድሮ ክረምትም የአቅመ ደካሞችን ቤት በመጠገን የጀመሩትን ስራ በአረንጓዴ አሻራና በሌሎች የልማት ስራዎች አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጿል፡፡   የመኖሪያ ቤታቸው የተጠገነላቸው ወይዘሮ ሙሉ አያሌው በበኩላቸው ፤ የተደረገልኝ የበጎ ፈቃድ ስራ ክረምቱን ያለ ስጋት ለማሳለፍ የሚያስችለኝ ነው በማለት ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በሕዝቦች መካከል ጠንካራ ማህበራዊ ትስስርን የመፍጠር ፋይዳው የጎላ ነው
Jul 11, 2026 257
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት አቅመ ደካሞችን ከመደገፍ ባለፈ በሕዝቦች መካከል ጠንካራ ማኅበራዊ ትስስር የመፍጠር ትልቅ ፋይዳ እንዳለው የብልፅግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጌቱ ወዬሳ ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጌቱ ወዬሳ፣ የዘንድሮውን የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል። የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት አቅመ-ደካሞችን ከመደገፍ ባለፈ፣ በሕዝቦች መካከል ጠንካራ ማኅበራዊ ትስስር የመፍጠር ትልቅ ፋይዳ እንዳለው በመግለጫቸው አብራርተዋል። በዘንድሮ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት 14 የተለያዩ በጎ ፈቃድ ተግባሮች ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል። የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በዋናነት የአቅመ ደካማና የእጅ አጠር ወገኖችን ቤት የመጠገን፣ የማደስና አዳዲስ የመኖሪያ ቤቶችን የመገንባት ስራዎችን ያካትታል ብለዋል። እንዲሁም ሀገር በቀልና የፍራፍሬ ችግኞችን በመትከል የአካባቢ ጥበቃና በእርሻ ሥራዎችን በትኩረት እንደሚከናወኑ ነው የተናገሩት። በተጨማሪ በሕዝብ አቅም እና አጋር አካል በማስተባበር፣ አዲስ የመማሪያ ክፍሎች ግንባታ እና የነባር መማሪያ ክፍሎች እድሳት እንደሚከናወን ገልጸዋል። በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍና የማዕድ ማጋራትን ጨምሮ ነጻ የምርመራ፣ የሕክምና አገልግሎት እንዲሁም የደም ልገሳ መርሐ-ግብር እንደሚካሄድ ገልጸዋል። ከተማን ምቹ እና ለኑሮ ተስማሚ እንዲሆን የሚያስችሉ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራዎች እንደሚከናወኑ ጠቁመዋል። በዚህ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት መርኃ ግብር ከ344 ሺህ 614 የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል።
ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ማህበረሰባዊ እሴቶችን በማጎልበት ለበጎ ዓላማ መተባበርን ያጠናክራል
Jul 11, 2026 410
ሐዋሳ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሃ ግብር ማህበረሰባዊ እሴቶችን በማጎልበት ለበጎ ዓላማ እርስ በርስ መተባበርን እንደሚያጠናክር ተሳታፊ ወጣቶች ገለጹ። መርሃ ግብሩ ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተውጣጡ ወጣቶች እውቀትና ባህላቸውን እንዲለዋወጡ ከማስቻሉም ባለፈ ሀገራዊ አንድነትን ለማጎልበት ትልቅ መድረክ መሆኑም ተመላክቷል። የዘንድሮ ወሰን ተሸጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሀግብር ''በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ'' በሚል መሪ ሀሳብ የፌደራልና የሲዳማ ክልል ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች በተገኙበት በሃዋሳ ከተማ ተጀምሯል።   መርሃ ግብሩ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ወሰን ሳይገድባቸው በበጎነት ህዝባቸውን ከማገልግል ባለፈ የባህል እሴቶችና ልምዳቸውን የሚለዋወጡበትን ምህዳር እየፈጠረ ነው፡፡ ኢዜአ ይህንኑ ተግባር ለማስቀጠል በተያዘው ክረምት ወደ ሥራ ከገቡ ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተሳታፊ ወጣቶች ጋር ቆይታ አድርጓል። ወጣቶቹ እንዳሉት፤ ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እርስ በርስ የመደጋገፍ ማህበረሰባዊ እሴትን ስለሚያጎለብት ሀገራዊ አንድነትን የሚያጠናክር ነው። ከወጣቶቹ መካከል ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወላይታ ሶዶ ከተማ የመጣችው ሳምራዊት አበራ፤የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መንግስት የማህበረሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያደርገውን ጥረት ያግዛል ብላለች። እሷም ባለፉት ጊዜያት በተግባሩ በመሳተፍ የህሊና እርካታ ማግኘቷንና ይህን ልምዷን በመያዝ በዘንድሮው ወሰን ተሸጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ላይ መሳተፏን ተናግራለች፡፡ ፕሮግራሙ ከማህበራዊ አገልግሎቱ ባለፈ የሌሎች አካባቢዎችን ባህልና የማሕበረሰብ እሴትን ለመረዳት እንዳስቻላትም ገልጻለች፡፡   ከድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የመጣው ወጣት ዑስማን ሃሰን በበኩሉ፤ መርሀ ግብሩ የተቸገሩ ወገኖችን የመደገፍ የቆየ ባህልን ለማዳበር የራሱ ድርሻ አለው ብሏል። ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የእርስ በርስ ግንኙነትን የሚያጠናክርና ወጣቶች እውቀትና ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ የሚያግዝ ነው ብሏል፡፡ ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ወጣቶች ማህበራዊ ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ ያስቻለ ነው ያለችው ደግሞ በሲዳማ ክልል የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዋ ወጣት ምህረት ፈለቀ ናት፡፡ በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ የትብብርና የአንድነት መንፈስ እሳቤን ወደ ተግባር ይበልጥ ለመለወጥ ተግታ እንደምትሰራም ተናግራለች፡፡ ከሐረር ከተማ የመጣው ወጣት ሙጀህዲን ረመዳን በበኩሉ፤ ወሰን ተሻጋሪ የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት የመደመር መንግስት የወለደው አዲስ እሳቤ መሆኑን ጠቅሶ የዚህ ትውልድ አካል በመሆኑ ደስተኛ መሆኑን ተናግሯል፡፡ ፕሮግራሙ የወጣቶችን የተደመረ አቅም ለመጠቀም የሚያስችልና የባህል ልውውጥና እና ትብብርን የሚያጠናክር እንደሆነም አንስቷል፡፡
የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ሥራዎች የእሳት አደጋና የጎርፍ ተጋላጭነትን ለመቀነስ አስችለዋል
Jul 10, 2026 1022
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):-የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ሥራዎች የእሳት አደጋና የጎርፍ ተጋላጭነትን ትርጉም ባለው መልኩ ለመቀነስ ማስቻላቸውን የአዲስ አበባ ከተማ የእሳትና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ገለጸ። ኮሚሽኑ የተቋማዊ አቅምን በማጠናከርና የአደጋ ስጋት አመራር ሥርዓቱን በማዘመን በአገር አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ተቋም ለመሆን እየሠራ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ የእሳትና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርትን በመገምገም በ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይም ዉይይት አካሂዷል።   የኮሚሽኑ ኮሚሽነር አሕመድ መሐመድ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፣ የመዲናዋ የኮሪደር ልማት አደጋን በዘላቂነት ለመቀነስ ዋነኛ መሣሪያ ሆኗል። የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ሥራዎች በመከናወናቸው መሰረታዊ ለውጥ መምጣቱን ጠቁመው፤ በተለይ ቀደም ሲል ለጎርፍ፣ ለእሳት አደጋና ለመሬት መንሸራተት ተጋላጭ የነበሩ አካባቢዎችን ደኅንነታቸው መጠበቁን ገልጸዋል።   በተጨማሪም ለተለያዩ ተቋማት የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠናዎች፣ የሙያ ምክር አገልግሎት፣ የቴክኒክ ድጋፍ እና የደህንነት መስፈርት ፍተሻዎችን በማከናወን በተቋማት ውስጥ የአደጋ መከላከል ባህል እንዲጠናከር ከፍተኛ ሥራ መሠራቱን ተናግረዋል፡፡ ኮሚሽኑም በቀጣይ የአደጋ መከላከል፣ የምላሽ አቅም ማጠናከር፣ ዲጂታል አሠራርን ማስፋፋት እና ከባለድርሻ አካላት ጋር ያለውን ትብብር በማጠናከር ለተሻለ የአገልግሎት ውጤት እንደሚሰራም ጠቅሰዋል፡፡   በአራዳ ቅርንጫፍ የኮሚሽኑ ባለሙያ የሆኑት ትዕግስት ተክለአብ ለኢዜአ እንዳሉት፣ ከማኅበረሰቡ ጋር በመደራጀት በብሎክና በወረዳ ደረጃ የቅድመ አደጋ መከላከል ሥራዎች ተከናውነው ጥሩ ውጤት ተመዝግቧል። ሌላው የኮሚሽኑ የአደጋ መከላከል ባለሙያ ማስረሻ ጥላሁን በበኩላቸው፣ አደጋዎች ሲከሰቱ በተቀመጠው መስፈርት መሠረት በፍጥነት በመድረስ አደጋዎችን የመቆጣጠር ሥራ በውጤታማነት መከናወኑን ገልጸዋል።   የኮሪደር ልማቱም ለአደጋ ተጋላጭ የነበሩ አካባቢዎችን በማልማት የኮሚሽኑን የአደጋ ቅነሳ ሥራ እንዳገዘ ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ በተፈጥሯዊና በሰው ሠራሽ አደጋዎች ላይ የመከላከልና የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች በስፋት መከናወናቸው ተጠቁሟል፡፡  
የሕክምና ማዕከሉ ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ ትልቅ አቅም ይፈጥራል
Jul 10, 2026 1024
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):-"አዲስ የላቀ የሕክምና ማዕከል" ዘመናዊና ጥራቱን የጠበቀ የሕክምና አገልግሎትን ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዛሬው ዕለት የራስ ደስታ ዳምጠው ሆስፒታል ማስፋፊያ የሆነውን "አዲስ የላቀ የህክምና ማዕከል"ን መርቀው ስራ አስጀምረዋል።   በምረቃው ወቅት ከንቲባ አዳነች አቤቤ ባደረጉት ንግግር፤ ፕሮጀክቶችን በታቀደላቸው ጊዜ ጀምሮና በፍጥነት አጠናቆ ለአገልግሎት ማብቃት የከተማ አስተዳደሩ መለያ ባህል መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ ከሠራባቸው ማኅበራዊ ዘርፎች መካከል የጤናው ዘርፍ ተጠቃሽ መሆኑንም አክለዋል። በመዲናዋ የነበረውን የጤና አገልግሎት ለማሻሻል የበርካታ አዳዲስ ሆስፒታሎችና ጤና ጣቢያዎች ግንባታ መከናወኑን የጠቀሱት ከንቲባዋ፤ ከአዳዲስ ግንባታዎች ባሻገር በነባር የጤና ተቋማት ላይ ሰፊ የማስፋፊያና የእድሳት ሥራዎች መሠራታቸውን አስታውቀዋል። ይህም ለሕብረተሰቡ ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት ተደራሽ ከማድረግ አኳያ ትርጉም ያለው ለውጥ ማምጣቱን አመላክተዋል።   ከዚህ ቀደም ዜጎች በከፍተኛ ወጪ ወደ ውጭ ሀገር ሄደው ያገኟቸው የነበሩ የሕክምና አገልግሎቶች አሁን ላይ በከተማዋ መሰጠት መጀመራቸው ሀገሪቱን ከውጭ ምንዛሬና ዜጎችን ደግሞ ከእንግልት መታደጉን ጠቁመዋል፡፡ በጤናው ዘርፍ የተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት አዲስ አበባን የጤና ቱሪዝም ማዕከል እንድትሆን እያደረጋት እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡ ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው "አዲስ የላቀ ሕክምና ማዕከል" የሆስፒታሉን የአገልግሎት አሰጣጥ አድማስ በማስፋት፣ ለተገልጋዮች ምቹና ዘመናዊ ሆኖ መደራጀቱን ጠቅሰዋል፡፡ ማዕከሉ የራሱ የኦክስጅን ማምረቻን ጨምሮ ዘመኑን በዋጁ ልዩ ልዩ ዘመናዊ የሕክምና መሣሪያዎች የተደራጀ መሆኑን ጠቅሰው ከዚህ ቀደም የነበረውን ዘመናዊ እና ጥራቱን የጠበቀ የሕክምና አገልግሎት ይበልጥ ለማላቅና አቅምን ለማሳደግ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የማስፋፊያ ማዕከሉ ባለ ሰባት ወለል ሲሆን በ2 ሺህ 60 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ ነው፡፡
በሸገር ከተማ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መዘመኑ የህብረተሰቡን እርካታ አሳድጓል
Jul 10, 2026 530
ሸገር፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- በሸገር ከተማ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሰጣጥን በዘመናዊ መልኩ በማደራጀት፣ የነዋሪዎችን የአገልግሎት እርካታ ደረጃ ማሳደግ መቻሉ ተገለጸ። በሸገር ከተማ የአገልግሎት አሰጣጥ ክፍተትን በዘላቂነት ለመቅረፍ የአንድ ማዕከል አሰራርን ማስፋፋትና ማዘመን እንደ ዋነኛ የሪፎርም ስራ ተይዞ ሲከናወን ቆይቷል። የከተማው የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሥራ አስኪያጅ አቶ መኮንን አምቤ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ አሰራሩን ማዘመን ፈጣንና ጥራት ያለው ማህበረሰብ ተኮር አገልግሎትን በተግባር ለማረጋገጥ ማስቻሉን ገልጸዋል።   የአገልግሎቱ ዋና ዓላማ የተገልጋዮችን እንግልትና አድካሚ ምልልስ ማስቀረት መሆኑን የገለጹት ሥራ አስኪያጁ፤ አሰራሩ ምቹና ተደራሽ የሥራ ካባቢ በመፍጠር ማህበረሰቡ ቀልጣፋና ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኝ ማድረግ ማስቻሉን አስረድተዋል። በተለይም የአገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ በመደገፍ ወጪን መቀነስ፣ ለደንበኞች ምቹ ሁኔታን መፍጠር እና የተጠቃሚዎችን እርካታ ማሳደግ መቻሉን ገልጸው፤ ይህም ማህበረሰቡ በመንግስት ላይ ያለው እምነት ከፍተኛ ደረጃ ላይ እንዲደርስ ያደርጋል ብለዋል። አገልግሎቱን ይበልጥ ተደራሽና ፈጣን ለማድረግ በሶስት ዋና ዋና መንገዶች ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙም አክለው ገልጸዋል። ይህንን ተግባር ይበልጥ ስኬታማ ለማድረግም የአገልግሎት ማዕከላትን ማስፋፋት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ሲሆን፤ በዚህ ዓመት ብቻ ሶስት አዳዲስ ማዕከላት ተገንብተው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን ተናግረዋል። ወደ ማዕከሉ በመምጣት አገልግሎት ያገኙ ደንበኞች በበኩላቸው፤ በአንድ ማዕከል የሚሰጠው አገልግሎት ከአላስፈላጊ የወጪና የጊዜ ብክነት እንዳዳናቸው ገልጸዋል።   ከተጠቃሚዎች መካከል አቶ መሳይ ተሾመ፤ ቀደም ሲል አንድን ጉዳይ ለማስፈጸም በተለያዩ ቦታዎች በመመላለስ ጊዜያቸው ይባክን እንደነበር አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ግን ጉዳያቸው በአጭር ጊዜ ውስጥ እየተጠናቀቀላቸው እንደሚገኝ ተናግረዋል።   አቶ ጀማል መሀመድ በበኩላቸው፤ በዚህ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አማካኝነት ያለምንም እንግልትና ምልልስ የሚፈልጉትን አገልግሎት በአጭር ጊዜ ውስጥ ማግኘት መቻላቸውን ገልጸዋል።
ወደ እፎይታ የተሸጋገሩ የአዲስ አበባ ነፍሶች
Jul 10, 2026 598
በተስፋ ሰብዓዊነት ሰገነት ታጅበው፤ ወደ እፎይታ የተሸጋገሩ የአዲስ አበባ ነፍሶች ዝናብ ለብዙ ሰዎች የተፈጥሮ ውበት ነው። ለሌሎች ደግሞ የሰብል ተስፋ፣ የምድር ሕይወትና የአረንጓዴ ወቅት መገለጫ ነው። በአዲስ አበባ አንዳንድ ሰፈሮች ዝናብ ለቤተሰቦች የእፎይታ ሳይሆን የስጋት ምንጭ ነበር። የሚያፈሱ ጣሪያዎች፣ የተሰነጣጠቁ ግድግዳዎች፣ በውኃ የሚጥለቀለቁ ወለሎችና በአደጋ የተከበቡ መኖሪያዎች ለበርካታ ቤተሰቦች የዕለት ተዕለት የጭንቀት ምንጮች ነበሩ። የክረምት ወቅት ሲመጣ የቤት ዕቃዎችን ከደራሽ ጎርፍ ለመጠበቅ ከቦታ ወደ ቦታ ማንቀሳቀስ፣ ሕፃናት ከብርድና ከእርጥበት እንዲድኑ በርካታ ሌሊቶችን ነቅቶ መጠበቅ፣ የእሳትና የጎርፍ አደጋን በፍርሃት መጠበቅ የኑሯቸው አካል ሆኖ ቆይቷል። አንዳንዶች በየጊዜው በሚከሰቱ የእሳት አደጋዎች ስጋት ውስጥ ይኖሩ ነበር። ሌሎች ደግሞ በወንዝ ዳርቻና በተዳፋት ቦታ ስለሚኖሩ ለጤናና ለደህንነት የሚያሰጋ ሁኔታን በየዕለቱ ይጋፈጡ ነበር። ዛሬ ግን ያ ምስል በብዙ ስፍራዎች ተቀይሯል።   በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መሪነት በባለሀብቶች፣ በወጣቶች፣ በበጎ ፈቃደኞችና በማህበረሰቡ የጋራ ተሳትፎ የተከናወኑ የቤት ግንባታና የዕድሳት መርሃ ግብሮች ብዙዎችን ከአደገኛ መኖሪያ ወደ ዘመናዊና ምቹ ቤት በማሸጋገር ሰብዓዊ ውጤት እየስገኙ ይገኛል። እነዚህ ፕሮግራሞች የጡብና የሲሚንቶ ሥራ ብቻ አይደሉም። ሰብዓዊ ክብርን የሚያጎናጽፉ፣ ቤተሰቦችን በእፎይታ የሚያኖሩና የሕፃናትን የነገ ተስፋ የሚያለመልሙ ለውጦች ናቸው።   በዚህ ተጠቀሚ ከሆኑ የመዲናዋ ነዋሪዎች መካከል የልደታ ክፍለ ከተማ ነዋሪዋ ወይዘሮ ቤተልሔም አስፋ ይገኙበታል። እርሳቸው እንደሚገልጹት፣ ከዚህ ቀደም የሚኖሩበት ቤት እጅግ ያረጀ፣ በዝናብ ወቅት በከፍተኛ ሁኔታ የሚያፈስና ለኑሮ የማይመች ነበር። መኖሪያ ቤታቸው በወንዝ ዳርቻና በተዳፋት ቦታ ላይ የሚገኝ በመሆኑ ልጆቻቸው ለተለያዩ የጤና ችግሮች ይጋለጡ እንደነበርም ያስታውሳሉ። በበጎ ፈቃድ መርሃ ግብሩ አማካኝነት መሠረተ ልማት ወደተሟላለትና ለትራንስፖርት አመቺ ወደሆነ አካባቢ መሸጋገራቸው የቤተሰባቸውን ሕይወት እንደለወጠው ይናገራሉ። ዛሬ የዝናብ ወቅት የፍርሃት ምልክት አይደለም፤ የተረጋጋ ሕይወትን በሚያሳይ አዲስ ምዕራፍ ተተክቷል። ለሰው ልጅ መኖር አዳጋች ከነበረ ቤት ወጥተን ዛሬ በክብር ወደምንኖርበት ቤት ገብተናል፤ ይህ ለእኛ አዲስ የሕይወት ምዕራፍ ነው ይላሉ ወይዘሮዋ። የወይዘሮ ቤተልሔም ታሪክ ግን ብቸኛ አይደለም፤ በከተማው በበጎ ፈቃድ ፕሮግራም የተጠቀሙ ብዙ ቤተሰቦች ተመሳሳይ የአኗኗር ለውጥ ታሪክ ባለቤት ናቸው። በከተማው እየተከናወኑ በሚገኙ በጎ ፈቃድ መርሃ ግብሮች ተጠቃሚ የሆኑ በርካታ ዜጎች በሕይወታቸው ላይ ተጨባጭ ለውጥ መጥቷል።   ወይዘሮ ገነት ወልደማርያም ያለፉትን ዓመታት ሲያስታውሱ በጠባብና ለኑሮ በማይመች አካባቢ መኖር ለቤተሰባቸው በየቀኑ የሚደገም ፈተና እንደነበር ይናገራሉ። መተላለፊያ የሌለው፣ መሠረተ ልማት ያልተሟላለትና ለልጆች ዕድገት በማይመች አካባቢ ሕይወታቸውን አስቸጋሪ አድርጎት እንደነበር ያስታውሳሉ። ዛሬ ግን በመንግሥትና በበጎ ፈቃደኞች ትብብር የተገነባላቸው አዲስ መኖሪያ ቤት ከመጠለያነት ባለፈ ለቤተሰባቸው አዲስ የሕይወት ጅማሬ ሆኗል። በደህንነት የሚያድሩበት፣ በክብር የሚኖሩበትና ልጃቸው ያለ ፍርሃት የሚያድግበት ቤት ማግኘታቸውን በትልቅ የህይወት ስጦታነት ይገልጹታል። ይህ የቤት ግንባታ ፕሮግራም የግለሰብ ሕይወትን ብቻ የሚቀይር አይደለም። የቤተሰብ መረጋጋትን፣ የጎረቤት ትስስርንና የማህበረሰብ አንድነትን የሚያጠናክር ሰብዓዊ ኢንቨስትመንት መሆኑን የተጠቃሚዎቹ ታሪክ ያስረዳል።   የተገነባው ቤት ብቻ አይደለም፤ ተስፋችንም ነው የሚሉት ደግሞ ሌላኛው የበጎ ፈቃድ ዘመናዊ መኖሪያ መንደር ግንባታ ተጠቃሚ የሆኑት ሀርቆ ሀለጮ ናቸው። በመንግሥትና በበጎ ፈቃደኞች ትብብር የተደረገላቸው ድጋፍ ሕይወታቸውን እንደለወጠው ይናገራሉ። ለእርሳቸው የተገነባው ቤት የመጠለያ ቦታ ብቻ ሳይሆን፣ ማህበረሰቡ ከጎናቸው መቆሙን የሚያሳይ የክብር ማህተም ነው። የአቶ ሀርቆ ሀለጮ ታሪክ የሚያመለክተው አንድ ጠቃሚ እውነት አለ። ሰብዓዊ ድጋፍ በቁሳዊ እርዳታ ብቻ አይለካም። ተጠቃሚዎች እንደሚገልጹት፣ "እኛን የሚያስብ ማህበረሰብ አለ" የሚል ስሜት እንደተሰማቸውም ነው የሚናገሩት። ይህ ደግሞ ከግንባታው በላይ የሚዘልቅ ግዙፍ ሰብዓዊ ዋጋ አለው።   በተመሳሳይ ወይዘሮ ወጋየሁ ወርቁ የቀድሞ መኖሪያቸው በመጨናነቅና በየጊዜው በሚከሰቱ የእሳት አደጋዎች ስጋት የተሞላ ሕይወት ይመሩ እንደነበር ያስታውሳሉ። አሁን ግን በአዲሱ መኖሪያቸው የሚሰማቸው ስሜት ከፍርሃት ይልቅ መረጋጋት፣ ከጭንቀት ይልቅ ተስፋ ነው። የእነዚህ ቤተሰቦች ታሪክ በአዲስ አበባ የተከናወኑ የበጎ ፈቃድ ተግባራት የሚለኩት በተገነቡ ቤቶች ብዛት ብቻ ሳይሆን፣ በተለወጡ ሕይወቶች እና በተረጋጉ የአኗኗር ዘይቤዎችም ጭምር መሆኑን በግልጽ ያሳያል። የሰብዓዊነት ባህል ሲደረጅ ከሕንፃ ግንባታ የተሻገረን ትውልድ ያንፃል። በአዲስ አበባ የተከናወኑና የሚከናወኑ የበጎ ፈቃድ ተግባራት በቤት ግንባታ ብቻ የሚወሰኑ አይደሉም። የከተማዋ የምገባ ማዕከላት በየዕለቱ ለአረጋውያን፣ ለአቅመ ደካሞችና ለሌሎች ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ዜጎች የሚቀርቡ የምግብ ድጋፍ፣ የቤት ዕድሳትና ግንባታ፣ እንዲሁም የመኖሪያ ቤት ባለቤትነትን የሚያረጋግጡ ፕሮግራሞች በአንድ ላይ ተደምረው ለሺዎች ዜጎች አዲስ የሕይወት ምዕራፍ እየከፈቱ ነው። በየዓመቱ በሚከናወኑ የበጎ ፈቃድ መርሃ ግብሮች ወጣቶች ጉልበታቸውን፣ ባለሀብቶች ገንዘባቸውን፣ የማህበረሰብ አባላት ጊዜያቸውንና ሙያቸውን በማበርከት ሰብዓዊ አገልግሎትን ከንቅናቄ ወደ ባህል እንዲያድግ አስችለዋል። በዚህም ከቤት ግንባታ ባሻገር የመተሳሰብና የመረዳዳት ዕሴቶች በከተማዋ ይበልጥ እንዲጠናከሩ አድርገዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የሕብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አስራት ንጉሴ እንደገለጹት፣ ቀደም ሲል በከፊል የቤት ዕድሳት ላይ ያተኮረው አሠራር በአሁኑ ወቅት የከተማዋን የልማት አቅጣጫ በሚመጥን መልኩ ወደ ሙሉ የቤት ግንባታ ተሸጋግሯል። ይህም ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጎች፣ አረጋውያን፣ አካል ጉዳተኞች፣ አቅመ ደካሞችና ወላጅ አልባ ሕፃናት በቀዳሚነት ተጠቃሚ አድርጓል። በእርግጥም ልማት የሚለካው በሚገነቡ ሕንፃዎች ከፍታ ብቻ አይደለም። በዜጎች ሕይወት ላይ በሚመጣ ለውጥ እንጂ። በበጎ ፈቃድ መርሃ ግብሮች አማካኝነት ከሚያፈሱ ጎጆዎች ወደ ዘመናዊ መኖሪያዎች የተሸጋገሩ ቤተሰቦች፣ በምገባ ማዕከላት የዕለት ምግብ ዋስትና ያገኙ አረጋውያን፣ በተለያዩ ማህበራዊ ፕሮግራሞች ተደግፈው ተስፋን ያገኙ ዜጎች የዚህ እውነታ ሕያው ማሳያዎች ናቸው። ወይዘሮ ቤተልሔም፣ ወይዘሮ ገነት ወልደማርያም፣ አቶ ሀርቆ ሀለጮና ወይዘሮ ወጋየሁ ወርቁ ያካፈሉን ተሞክሮ የሚያሳየው አንድ ግልጽ መልዕክት ለሰው ልጅ ክብር የሚሰጥ መኖሪያ፣ የተረጋጋ የምግብ ዋስትናና የማህበረሰብ ድጋፍ ሲገናኙ የሚለወጠው ቤት ብቻ አይደለም፤ ሕይወት መሆኑን እንጂ። ስለዚህ በአዲስ አበባ የሚከናወኑ የበጎ ፈቃድ ተግባራት ከማህበራዊ ድጋፍ ባለፈ የከተማዋን የሰብዓዊ ልማት አቅጣጫ የሚያንፀባርቁ ናቸው። ከሚያፈስ ጎጆ ወደ ክብር መኖሪያ የተጀመረው ጉዞ፣ የጡብና የሲሚንቶ ታሪክ ሳይሆን የሰውን ክብር የመጠበቅ፣ ተስፋን የማደስና የማህበረሰብ አንድነትን በሚያጠናክር መልኩ እየቀጠለ ይገኛል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከአንድ ነጥብ አራት ሚሊዮን በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ይሆናሉ
Jul 10, 2026 380
ደብረ ማርቆስ ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- በምስራቅ ጎጃም ዞን በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከአንድ ነጥብ አራት ሚሊዮን በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ የዞኑ ሴቶች ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ ገለፀ፡፡ የመምሪያው ኃላፊ ወይዘሮ አሞኘሽ መሀመድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤በክረምቱ የበጎ ፈቃድ ስራ ከ 636 ሺህ በላይ ወጣቶችና የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ይሳተፋሉ።   በዚሁ ወቅት በሚካሔደው የበጎ ፈቃድ ስራም ከአንድ ቢሊየን ብር በላይ ግምት ያለው የልማት ስራ እንደሚከናወንም ነው የተናገሩት። በዚህም ከአንድ ነጥብ አራት ሚሊዮን በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በ17 የስራ ዘርፎች የሚካሄደው የበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ ከ 2 ሺህ 552 ዩኒት በላይ ደም መለገስን ጨምሮ ከሶስት ሺህ በላይ የአረጋዊያንና የአቅመ ደካሞች ቤቶችን በአዲስ የመገንባትና የመጠገን ስራ እንደሚከናወን አስረድተዋል። በዚሁ ወቅት ከ260 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል፣ በአካባቢ ፅዳትና ውበት ጥበቃ፣ በትምህርትና ሌሎች ተግባራት በጎ ፈቃደኞችን በማሰማራት ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል።   ‎በዞኑ የአንደድ ወረዳ የአንበር ከተማ ነዋሪ ወጣት ደግሰው ደሴ፤ ባለፉት ዓመታት በክረምትና የበጋ በጎ ፈቃድ አገልግሎት በመሰማራት ህብረተሰቡን እያገለገለ መሆኑን ተናግሯል። በአሁኑ ወቅትም በተለያዩ የበጎ ፈቃድ ስራዎች ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ አጠናክሮ መቀጠሉን ነው የሚናገረው። የጎዛምን ወረዳ የጥጃን ቀበሌ ነዋሪ አቶ መልስ ገናነው በበኩላቸው፤ በክረምቱ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የአቅመ ደካሞችን እርሻ በመዝራት፣ በማረምና የመንከባከብ ስራ ላይ መሰማራታቸውን ተናግረዋል። በዞኑ ባለፈው ዓመት በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ሰጭዎች ለተለያዩ ተግባራት ይወጣ የነበረ ከ900 ሚሊዮን ብር በላይ የመንግስት ገንዘብ ማዳን መቻሉም ተመላክቷል።
በደም እጦት ምክንያት ህይወታቸውን የሚያጡ እናቶችና ዜጎችን ለመታደግ የበጎ ፈቃድ ስራችንን አጠናክረን እንቀጥላለን
Jul 10, 2026 338
ደብረ ብርሃን፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- በደም እጦት ምክንያት ህይወታቸውን የሚያጡ እናቶችና ዜጎችን ለመታደግ የደም ልገሳ ተግባርን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በደብረ በብርሃን ከተማ የሚገኙ በጎ ፈቃደኞች ገለጹ። በሰሜን ሸዋ ዞንና በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ10 ሺህ ዩኒት በላይ ደም በመሰብሰብ ጥቅም ላይ እንዲውል ማድረጉን የደብረ ብርሃን ደም ባንክ አገልግሎት አስታውቋል። ከበጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች መካከል ወይዘሮ ሐይማኖት ተክሌ፤ ለአራተኛ ጊዜ ደም በመለገስ የእናቶችና ህፃናትን ህይወት ለመታደግ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ለኢዜአ ገልጸዋል፡፡ በተለይም በወሊድ ወቅት በደም እጥረት ምክንያት ህይወታቸውን የሚያጡ እናቶችን ለመታደግም የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በማስተባበር ደም እንዲለግሱ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።   ሌላው ደም ለጋሽ ወጣት አበባው በላይ በበኩሉ፤ በሚተካ ደም የማይተካ ህይወትን ማትረፍ ከሚሰጠው የመንፈስና የህሊና እርካታ በላይ የሚያስደስት የበጎ ፈቃድ ስራ የለም ሲል ነው የገለጸው። በቅርቡም ለ7ኛ ጊዜ ደም መለገሱን ጠቁሞ ከራሱ ባሻገር በህክምና ተቋማት የደም እጥረት እንዳያጋጥም በደም ልገሳ የበጎ ፈቃድ ስራዎች ላይ እንደሚሳተፍ አስታውቋል። የደብረ ብርሃን ደም ባንክ አገልግሎት ስራ አስኪያጅ አቶ በዛብህ አባይነህ ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በጎ ፈቃደኞችን በማስተባበር ከ10 ሺህ ዩኒት በላይ ደም በመሰብሰብ ጥቅም ላይ እንዲውል መደረጉን ተናግረዋል።   በአዲሱ የ2019 በጀት ዓመትም 10 ሺህ 500 ዩኒት ደም ከለጋሾች በመሰብሰብ ለ20 ጤና ተቋማት ለማቅረብ ጥረት እንደሚደረግ አስገንዝበዋል። የደም ልገሳ እቅዱን ስኬታማ ለማድረግም ከወጣቶች በተጨማሪ የኃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ሌላው ማህበረሰብ በንቃት እንዲሳተፍም ጥሪ አቅርበዋል።
በአማራ ክልል ከሁለት ዓመት በታች የሆኑ ህጻናት የመቀንጨር ምጣኔ ተጨባጭ በሆነ መልኩ ቀንሷል
Jul 10, 2026 392
ባህር ዳር ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- በአማራ ክልል መቀንጨርን ለመከላከል በተደረገ መጠነ ሰፊ ርብርብ ከሁለት ዓመት በታች ባሉ ህጻናት ላይ ያጋጥም የነበረው የመቀንጨር ሁኔታ በተጨባጭ መልኩ መቀነሱን በክልሉ የሰቆጣ ቃል-ኪዳን ፕሮግራም ማስተባበሪያ አመለከተ። በስርዓተ ምግብ አጠቃቀም፣ አመራረትና የአመጋገብ ባህል ላይ የሚዲያ ባለሙያዎችን ያሳተፈ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ በባህር ዳር ከተማ ተካሄዷል። በክልሉ የሰቆጣ ቃል ኪዳን ፕሮግራም ማስተባበሪያ የማህበረሰብ ባህሪ ለውጥ ተግባቦት አማካሪ አቶ ጋሻው አዳነ እንደገለጹት፤ ፕሮግራሙ በተከዜ ተፋሰስ በሚገኙ ዞኖችና ወረዳዎች ላይ ትኩረት አድርጎ እየሰራ ይገኛል። በተፋሰሱ በሚገኙ 27 ወረዳዎች ተጀምሮ የነበረውን የስርዓተ ምግብ ማሻሻል ትግበራ አሁን ላይ ወደ 133 ወረዳዎች በማስፋት ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝም አስረድተዋል። በዚህም ለስርዓተ ምግብ እጥረት መንስኤ የሆኑት የምግብ ግብዓት አቅርቦት ችግር፣ የአመራረት፣ የአጠቃቀምና የግንዛቤ ክፍተቶችን ለመፍታት በትኩረት መሰራቱን ገልጸዋል። እንዲሁም የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው አትክልትና ፍራፍሬ፣ እንቁላል ጣይ ዶሮዎችንና እንስሳትን ለነፍሰ ጡርና ለሚያጠቡ እናቶች በመስጠት የተከናወነው ስራ ውጤት ማስገኘቱን አብራርተዋል። ከአመራረት ጀምሮ አሰባጥሮ እስከ መመገብ ያለውን ችግር ለመቅረፍ በተሰራው ስራ፣ ቀደም ሲል 53 በመቶ ደርሶ የነበረውን ከሁለት ዓመት በታች የህጻናት መቀንጨር ምጣኔ አሁን ላይ ወደ 27 በመቶ ዝቅ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። ይህም ጤንነቱ የተጠበቀ፣ አእምሮው የዳበረና አምራች ትውልድ በመፍጠር የነገ ሀገር ተረካቢ ዜጋን ከመሰረቱ የመገንባት ስራው ስኬት እያስመዘገበ ለመሆኑ ትልቅ ማሳያ መሆኑን አስረድተዋል። በተለይም አንዲት እናት ነፍሰ ጡር ከሆነችበት ዕለት አንስቶ ባሉት ወሳኝ አንድ ሺህ ቀናት ውስጥ የእርሷንና የህጻኑን አመጋገብ በማሻሻል ችግሩን መቅረፍ እንደሚቻል በተከናወኑ ተግባራት ማረጋገጥ መቻሉን ገልጸዋል። የሚዲያ ባለሙያዎችም ቃል ኪዳኑ እያከናወነ ያለውን ተግባር በአግባቡ በመረዳት፣ በተገኙ ለውጦችና ተሞክሮዎች ላይ በማተኮር ለህብረተሰቡ ግንዛቤ በመፍጠር ረገድ የድርሻቸውን እንዲወጡም አሳስበዋል።   የአማራ ክልል መንግስት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አባይ መንግስቴ በበኩላቸው፤ በክልሉ የሚታየው የተመጣጠነ ምግብ እጥረት ችግር የምርት ማነስ ሳይሆን የግንዛቤ ክፍተት ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። ይህን ችግር በመሰረታዊነት ለመቀየርም መንግስት የቃልኪዳን ስምምነቱን ወደ ስራ በማስገባት ዘርፈ ብዙ ተግባራትን በማከናወን ለውጥ እንዲመጣ ማስቻሉን ኃላፊው አስረድተዋል። የሚዲያ ተቋማትና ባለሙያዎችም እየተሰራ ያለውን ስራ በዘገባዎቻቸው ተንትነው በማስረዳት፣ ችግሩን ሙሉ በሙሉ በመቅረፍ ጤናማ ትውልድ ለመገንባት የሚደረገውን ጥረት ማገዝ እንደሚገባቸው አሳስበዋል። ለቃል ኪዳኑ ተግባር ማስፈጸሚያም በራሱ በፕሮግራሙ፣ እንዲሁም በፌደራልና በክልል መንግስታት አማካኝነት በየዓመቱ ከ1 ነጥብ 13 ቢሊዮን ብር በላይ እየተመደበ መሆኑም ተመላክቷል።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት በክህሎትና በስነ- ምግባር የታነጹ ዜጎችን በማፍራት ረገድ ውጤታማ ስራዎች ተከናውነዋል 
Jul 10, 2026 363
ጋምቤላ ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):-ባለፉት የለውጥ ዓመታት በትምህርት ጥራት ላይ በተከናወኑ ተግባራት፣ በክህሎትና በሥነ-ምግባር የታነጹ ዜጎችን በማፍራት ረገድ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን የጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ተገኝተው የ2018 በጀት ዓመትን አስመልክተው በሰጡት ማብራሪያ፤ ባለፉት አምስት ዓመታት በትምህርት ዘርፉ በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን መግለጻቸው ይታወሳል። በተለይም ከቅድመ-መደበኛ ጀምሮ በሁሉም የትምህርት ደረጃዎች በርካታ የፖሊሲና የሪፎርም ሥራዎች መከናወናቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በዘርፉ ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን አብራርተዋል። የጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ምሁራንም ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በየደረጃው የሚሰጡ የሥልጠና መመዘኛዎችን ጨምሮ በተከናወኑት የሪፎርም ሥራዎች በትምህርት ጥራት ላይ ተጨባጭ ለውጥ እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሽብሩ ዘሪሁን (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት በትምህርት ዘርፉ የተከናወኑ የለውጥ ሥራዎች በተለይም በትምህርት ጥራት ላይ ተጨባጭ ውጤቶች እንዲመዘገቡ አስችለዋል። የሪፎርም ሥራዎችን ጨምሮ የቅድመ-ምረቃ መውጫ፣ የድኅረ-ምረቃ መግቢያና የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተናዎች በዩኒቨርሲቲዎች መሰጠታቸው በትምህርት ጥራት ላይ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ለውጥ ማምጣቱን ገልጸዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በተከናወኑት የለውጥና የሪፎርም ስራዎች በክህሎት፣ በዕውቀትና በስነ-ምግባር የታነጹ ዜጎችን በማፍራት ረገድ ውጤታማ ተግባራት እንዲከናወኑ አስችለዋል ብለዋል። የጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ፣ የምርምር፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዚዳንት አማካሪ ተባባሪ ፕሮፌሰር ጀምበሩ ዓለሙ በበኩላቸው፤ እንደ ሀገር በዘርፉ በተከናወኑት የስልጠናና ለውጥ ስራዎች በትምህርት ጥራት በርካታ ስኬቶች ተገኝተዋል ብለዋል። በተለይም የዩኒቨርሲቲ የመውጫ ፈተናን ጨምሮ በአጠቃላይ በየደረጃው የሚሰጡት የክልልና ሀገር አቀፍ መመዘኛዎች ለትምህርት ጥራት የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ተናግረዋል። ቀደም ሲል ወደ ዩኒቨርሲቲው ይገቡ የነበሩ ተማሪዎች ከፍተኛ የአቅም ችግር እንደነበረባቸው ያስታወሱት ተባበሪ ፕሮፌሰሩ፤ አሁን ላይ ጠያቂና ተመራማሪ ተማሪዎች እየመጡ መሆናቸውን ገልጸዋል። ቀደም ሲል የዩኒቨርሲቲ መውጫ ፈተና ሲጀመር የተማሪዎች መጠነ ማለፍ 25 ከመቶ ብቻ የነበረ ሲሆን አሁን ላይ ወደ 91 ነጥብ 2 ከመቶ ከፍ ማለቱን ተባባሪ ፕሮፌሰሩ በማሳያነት ጠቅሰዋል።
የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በሚያከናውኗቸው ተግባራት የማህበረሰብ ተጠቃሚነትን ሊያጎለብቱ ይገባል
Jul 9, 2026 1311
ሰመራ፤ሐምሌ 2/2018 (ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል የሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በሚያከናውኗቸው ተግባራት የማህበረሰብ ተጠቃሚነትን ሊያጎለብቱ እንደሚገባ የክልሉ ገንዘብ ቢሮ አመለከተ። በአፋር ክልል የሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች በአፈፃፀም ሪፖርትና በቅንጅታዊ ተግባራት ዕቅድ ላይ በሰመራ ከተማ ውይይት አድርገዋል።   በወቅቱም የአፋር ክልል ገንዘብ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ደረሳ መሐመድ እንደገለፁት፤ በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የሚያከናውኗቸው ተግባራት የማህበረሰብ ተጠቃሚነትን ሊያጎለብቱ ይገባል። ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ ድርጅቶቹ እርስ በርስ ተናበውና ተቀናጅተው ሊሰሩ እንደሚገባ አመልክተዋል። ባለፈው በጀት ዓመት በክልሉ ድርጅቶቹ 60 ዋና ዋና ፕሮጀክቶችን ያከናወኑ መሆኑን ገልጸው ለፕሮጀክቶቹም በአጠቃላይ 6 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ወጪ መደረጉን አስረድተዋል። ከፕሮጀክቶቹ መካከል 18ቱ በጤናና በሥነ-ምግብ ዘርፎች ላይ ያተኮሩ መሆናቸውን አብራርተዋል። ድርጅቶቹ በሚያከናውኗቸው የልማት ሥራዎች የአካባቢውን ማኅበረሰብ ተጨባጭ ፍላጎት ከማገናዘብ ባለፈ የሥራ ዕድሎችን ማመቻቸት እንደሚገባቸውም ምክትል ኃላፊው አመልክተዋል። በክልሉ በተከናወኑ የትምህርት፣ የጤና፣ የውሃና ሌሎች ዘርፎች ድርጅቶቹ ያበረከቱት አስተዋጽኦ ጉልህ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህንኑ ኅብረተሰብን ማዕከል ያደረገ ድጋፋቸውን አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም አሳስበዋል።   የ"ፍሬንድሺፕ ሰፖርት አሶሴሽን" ፕሮግራም ማናጀር ወይዘሮ የማ ዳንኤል በበኩላቸው፤ ፕሮግራሙ በጤና፣ በውሃና በሰላም ግንባታ ዘርፎች ላይ የተለያዩ ሥራዎችን ማከናወኑን ገልጸው የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማላቅ በትጋት እንደሚሰሩም ተናግረዋል። በክልሉ በተለያዩ ወረዳዎች በሕዝብና እንስሳት ጤና ዘርፎች እንዲሁም በውሃ ላይ በመሰማራት የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ያጎለበቱ በርካታ ተግባራትን እንዳከናወኑ የገለጹት ደግሞ "ኮፕ" (COOP) በተሰኘው የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅት የአፋር ቅርንጫፍ አስተባባሪ አቶ መሐመድ ጎንፍሬ ናቸው።   በበጀት ዓመቱ ድርጅቶቹ በክልሉ በሚገኙ ስድስት ዞኖች ውስጥ በስፋት ተሰማርተው፣ ማኅበረሰብ ተኮር የሆኑ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን በስኬት ማከናወናቸውም ተገልጿል።
የሃይማኖት ተቋማት ለአገር ሰላምና አብሮነት የጀመሩትን ተቀራርቦ የመሥራት በጎ ልምድ ሊያጠናክሩ ይገባል
Jul 9, 2026 828
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2 /2018(ኢዜአ) ፦ የሃይማኖት ተቋማት ለአገር ሰላምና አብሮነት የጀመሩትን ተቀራርቦ የመሥራት በጎ ልምድ ሊያጠናክሩ እንደሚገባ የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ኸይረዲን ተዘራ (ዶ/ር) አመለከቱ። የሰላም ሚኒስቴር በህዝቦች መካከል አብሮነትን ማጠናከርና ዘላቂ ሰላም ግንባታን በተመለከተ ከሃይማኖት ተቋማት መሪዎች እና ተወካዮች ጋር ውይይት አካሂዷል።   ሚኒስትር ዴኤታው በወቅቱ እንዳሉት፤ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የተሰጠውን ተልዕኮ መነሻ በማድረግ እንዲሁም የሃይማኖት ተቋማት ለሰላም ግንባታና ለብሔራዊ መግባባት ያላቸውን አይተኬ ሚና ከግምት ውስጥ በማስገባት በቅርበት እየሠራ ይገኛል። ይህ ዓይነቱ ትብብርም የሃይማኖት አባቶች በሥነ-ምግባር የታነጸ ትውልድ በመቅረጽ ረገድ የጎላ ድርሻ እንዲወጡና የሕዝቦችን ሰላምና አብሮነት እንዲያጎለብቱ ለማስቻል ያለመ መሆኑንም ገልጸዋል። መንግሥት የሃይማኖት በዓላት በሰላም ተከብረው እንዲጠናቀቁ በትኩረት እየሠራ እንደሚገኝም ሚኒስትር ዴኤታው አስገንዝበዋል። ይህንን ሂደት ይበልጥ ቀልጣፋ ለማድረግም በትኩረት እንደሚሠራም አክለው ተናግረዋል። መንግሥት ከሃይማኖት ተቋማት ጋር ያለው ግንኙነት ሰላማዊ፣ በመከባበር ላይ የተመሠረተና ሕገ-መንግሥታዊ የሃይማኖትና የመንግሥትን መለያየት መርህ የጠበቀ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል።   በተቋማቱ መካከል ያለው ሰላምና መልካም ግንኙነት መሻሻሉን ጠቁመው፤ አንዱ ተቋም ከሌላው ጋር በአብሮነትና መደጋገፍ ችግሮቹን ለመፍታት የሚያሳየው አጋርነት እያደገ መምጣቱ የሚበረታታና የሚያስመሰግን መሆኑንም ነው የገለጹት። ሁሉም የሃይማኖት ተቋማት ለተከታዮቻቸው በአብሮነት፣ በጋራ ተከባብሮ መኖር እና በወሳኝ ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የጀመሩትን ተቀራርቦ የመስራት በጎ ልምድ አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጥሪ አስተላልፈዋል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የሃይማኖት መሪዎች በቀጣይ ትኩረት በሚሹ ጉዳዮች ላይ ሀሳባቸውን አንስተዋል። ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በቅንጅት መሥራታቸው በበርካታ ጉዳዮች ዙሪያ በጋራ ለመንቀሳቀስ ዕድል መፍጠሩን ገልጸው ይህንን በጎ ሂደት አጠናክረው እንደሚቀጥሉ መናገራቸውን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የመንግሥት አዲሱ የቤት ልማት ዕቅድ ለዜጎች ትልቅ እፎይታ የሚሰጥ ነው
Jul 9, 2026 387
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/ 2018(ኢዜአ):-መንግሥት በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ውስጥ በመላ ሀገሪቱ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ መኖሪያ ቤቶችን ለመገንባት ማቀዱ ለዜጎች ትልቅ እፎይታን የሚሰጥ ነው ሲሉ አስተያየታቸውን የሰጡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸው፤ የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ ሰፊ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ የቤት ልማት ጉዳይ ከጉባ ብስራቶች መካከል አንዱ መሆኑንና መንግሥት በከፍተኛ ትኩረት እንደሚሠራበት ተናግረዋል። በዚህም መሠረት ባለፉት ሰባት ዓመታት ውስጥ ብቻ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ቤቶች መገንባታቸውን ጠቅሰዋል። በቀጣዮቹ አምስት ዓመታትም 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶችን በመንግሥት፣ በግል၊ በመንግሥትና በግል አጋርነት እንዲሁም በሌሎች አማራጮች ለመገንባት ዕቅድ ተይዞ ሰፊ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህንን ስኬታማ ማድረግ የሚያስችል አዲስ የመኖሪያ ቤት ፖሊሲ በሚኒስትሮች ምክር ቤት መጽደቁን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ግንባታውን በገጠርና በከተማ ለማፋጠን በትጋት እየተሠራ መሆኑን አስረድተዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ የግንባታ ፍጥነትን ለመጨመርም እንደ 3ዲ ያሉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ወደ ሥራ እየገቡ መሆኑን ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቤት ልማት ዙሪያ የሰጡትን ማብራሪያ በተመለከተ ኢዜአ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች እንዳመለከቱት፤ ይፋ የተደረገው የቤት ልማት ሥራ ተስፋ ሰጪ መሆኑን ገልጸዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡት ነዋሪዎች መካከል አቶ ተሾመ ረጎ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት ነዋሪዎችን እየፈተነ ያለው የመኖሪያ የቤት አቅርቦት ችግር በዘላቂነት ምላሽ ሊያገኝ ይገባል፡፡ መንግሥት ይህንን ችግር ለመቅረፍ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የሰጠው ትኩረትና ያከናወናቸው ተግባራት በርካታ ዜጎችን የቤት ባለቤት ማድረግ የቻለ ቢሆንም፣ አሁንም ቢሆን የችግሩ ስፋት ከፍተኛ መሆኑን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምክር ቤቱ ያደረጉት ንግግር መንግሥት የቤት ችግሩን ከመሠረቱ ለመፍታት ያለውን ቁርጠኝነት ይበልጥ ያረጋገጠ በመሆኑ ለነዋሪው ትልቅ ተስፋ የሰጠ ነው ብለዋል። ሌላኛው የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ መጋቢ ሥርዓት አበራ ግሩም በበኩላቸው፤ አዲስ አበባ የሀገሪቱ ዋና ከተማ እንደመሆኗ መጠን ሰፊ የቤት ልማት ግንባታ እንደሚያስፈልጋት ጠቁመዋል። ይህንን ችግር ለመቅረፍ መንግሥት ልዩ ትኩረት መስጠቱ እንዳስደሰታቸው ገልጸው፤ በቀጣይ ሊገነቡ የታሰቡት ቤቶች ለመንግሥት ሠራተኛውና ዝቅተኛ ገቢ ላለው የሕብረተሰብ ክፍል ትልቅ እፎይታ የሚሰጡ በመሆናቸው ግንባታው ሊፋጠን እንደሚገባ ተናግረዋል። የመዲናዋ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ዝናሽ ተሰማ በበኩላቸው፤ አሁን ያለውን ነባራዊ የመኖሪያ ቤት እጥረት ለመቅረፍ የታቀደው ይህ የቤት ልማት ዕቅድ ለከተማዋ ነዋሪዎች ትልቅ እፎይታ የሚሰጥና የሚያስደስት መሆኑን ተናግረዋል። መንግሥት በቀጣይ ያቀደው ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ቤቶች ግንባታ እጅግ ወሳኝ እርምጃ መሆኑን የጠቀሱት ደግሞ አቶ ማስረሻ አፈወርቅ ናቸው። የቤት ልማቱ ተደራሽነትና ቀጣይነት እንዲኖረው ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስታውቀዋል።
አዲሱ ስትራቴጂክ ዕቅድ የሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ ተልዕኳችንን በገለልተኝነትና በተጠያቂነት ለማከናወን ዳግም ቃል የምንገባበት ነው
Jul 9, 2026 1093
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2 /2018(ኢዜአ)፦ አዲሱ ስትራቴጂክ ዕቅድ የሰብአዊ መብቶች ጥበቃ ተልዕኳችንን በገለልተኝነትና በተጠያቂነት ለማከናወን ዳግም ቃል የምንገባበት ነው ሲሉ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ ገለጹ። የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በቀጣይ አምስት ዓመታት የሚመራበትን ስትራቴጂክ ዕቅድ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በዛሬው ዕለት ይፋ አድርጓል።   የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ በዚሁ ወቅት፤ ኮሚሽኑ በአዋጅ የተሰጠውን ሰብዓዊ መብቶችን የማስጠበቅ፣የማስፋፋትና የመከታተል ሥልጣንና ኃላፊነት በተሟላ ሁኔታ ለመወጣት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ባለፉት አምስት ዓመታት በሀገር አቀፍ ደረጃ ሰብዓዊ መብቶች የተጠበቁ፣ የተከበሩና የተሟሉ እንዲሆኑ ለማድረግ ባከናወናቸው ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን በተደረገ ግምገማ ማረጋገጥ መቻሉን ተናግረዋል። ኮሚሽኑ ከዚህ በፊት ይመራበት የነበረው ስትራቴጂክ ዕቅድ የትግበራ ጊዜ መጠናቀቁን ተከትሎ፣ አዲሱ ስትራቴጂክ ዕቅድ ይፋ መደረጉንም አብራርተዋል። ይህ ስትራቴጂክ ዕቅድ በርካታ አዳዲስ የለውጥ ሐሳቦችን እንዳካተተ በመጠቆም፤ከዚህ በፊት ከነበረው በበለጠ ሁኔታ የሚወጡ ሕጎችና ፖሊሲዎች ሰብዓዊ መብቶችን ያከበሩና የተጣጣሙ እንዲሆኑ ትኩረት ማድረጉን ገልጸዋል። ዜጎች ከልጅነታቸው ጀምሮ ስለ ሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ ግንዛቤ ይዘው እንዲያድጉ ለማድረግም፣የሰብዓዊ መብቶች ትምህርትን በሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ለማካተት እንደሚሠራም ጠቁመዋል። በተጨማሪም በሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ ላይ የሚሠራ የጥናትና ምርምር ክፍል እንዲሁም ኢንስቲትዩት ለማቋቋም መታቀዱን ዋና ኮሚሽነሩ ተናግረዋል። ለዚህም ተግባራዊነት ኮሚሽኑ ከባለድርሻ አካላትና ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በትብብር እንደሚሠራ አረጋግጠዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል መስፍን እርካቤ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የሰብአዊ መብት ድንጋጌዎችን ተቀብላ ያጸደቀች ሀገር ናት ብለዋል።   ባለፉት አምስት ዓመታት ቋሚ ኮሚቴው ባደረገው ክትትል ኮሚሽኑ ተጨባጭ የሰብዓዊ መብት ጥበቃ ሥራዎችን ማከናወን መቻሉን ማረጋገጥ ተችሏል ነው ያሉት። በሴቶችና ህጻናት መብቶች፤ በህግ ታራሚዎች አያያዝ፣ በስደተኞች አያያዝ፣ በአካል ጉዳተኞች መብት አጠባበቅ ዙሪያ በርካታ ተግባራት ማከናወኑን አመላክተዋል። አዲሱ ስትራቴጂክ እቅድ ኮሚሽኑ ስራውን ለማላቅ የሚያስችለው መሆኑን ጠቁመው፤ ቋሚ ኮሚቴው ለስትራቴጅክ እቅዱ መሳካት ክትትልና ድጋፍ በማድረግ የበኩሉን ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል።   ስትራቴጂክ ዕቅዱ ሰብዓዊ መብቶችን ይበልጥ ለማስጠበቅና የፍትሕ ተደራሽነትን ለማስፋት አይነተኛ ሚና እንዳለው የገለጹት ደግሞ የአዲስ አበባ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ተወካይ ነብይ ተካ ከበደ ናቸው፡፡ ለእቅዱ ተግባራዊነት ሃይማኖት ተቋማት የበኩላቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል፡፡
መንግሥት በየጊዜው የሚያቀርባቸው የሰላም ጥሪዎች ለሀገራዊ መረጋጋት ያላቸው ፋይዳ ከፍተኛ ነው - የሀገር ሽማግሌዎች
Jul 9, 2026 335
ጅግጅጋ፤ ሐምሌ 2/2018(ኢዜአ)፦ መንግሥት በየጊዜው የሚያቀርባቸው የሰላም ጥሪዎች ለሀገራዊ መረጋጋትና ዘላቂ ሰላም ያላቸው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑን የሶማሌ ክልል የሀገር ሽማግሌዎች አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ መስጠታቸው ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸውም መንግስት ለዘላቂ ሰላም፣ ለንግግርና አብሮ ለመስራት ቁርጠኛ መሆኑን በማብራሪያቸው አስረድተዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩን ማብራሪያ መሰረት በማድረግ ኢዜአ ያነጋገራቸው የሶማሌ ክልል የሀገር ሽማግሌዎች፤ መንግሥት በየጊዜው የሚያቀርባቸው የሰላም ጥሪዎች ለሀገራዊ መረጋጋትና ዘላቂ ሰላም ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል ሱልጣን መሀሙድ ፋረህ፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምክር ቤቱ ያቀረቡት የሰላም ጥሪ መንግሥት ለሀገር ሠላም ያለውን ቁርጠኝነትና ሆደ ሰፊነት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ረጅም ታሪክ ያላት ጥንታዊ ሀገር እና የህዝቧም የሰላም እሴት ጠንካራ መሆኑን የጠቀሱት የሀገር ሽማግሌው፤ በሀገሪቱ የሚያጋጥሙ ማናቸውንም አለመግባባቶችና ቅራኔዎች በውይይትና በምክክር መፍታት እንደሚቻል አጽንኦት ሰጥተዋል። ሰላም ከምንም በላይ ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ መሆኑን በመጥቀስ፤ የሀሳብ ልዩነት ያላቸው አካላት የመንግስትን የሰላም ጥሪ በቅንነት በመቀበል፣ ሀሳብና ጥያቄዎቻቸውን በውይይት መፍታት እንደሚችሉ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለሁሉም በቂ መሆኗንና ግጭት ልማትን የሚያደናቅፍ መሆኑን ጠቅሰው፤ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ሰላም እንዲረጋገጥ እያንዳንዱ አካል የመንግስትን የሰላም ጥሪ በመስማትና ወደ ሰላማዊ ህይወት በመመለስ የድርሻውን መወጣት እንዳለበት ገልጸዋል። ሌላው የአገር ሽማግሌ አቶ አብዲ ኡመር በበኩላቸው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ልዩነቶች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱና ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን መንግሥት እያደረገ ያለውን ጥረት በተደጋጋሚ መግለጻቸው የሚደገፍ መሆኑን ተናግረዋል። በሀገሪቱ አስተማማኝ ሰላምና ልማት እንዲመጣ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች ሊወጡት የሚገባው ሚና ከፍተኛ መሆኑንም አቶ አብዲ አጽንኦት ሰጥተዋል። የሰላም ጉዳይ የመንግሥት ብቻ ኃላፊነት አለመሆኑን የጠቆሙት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ አሊ ሙሀመድ ናቸው። ለሀገር ሰላም መረጋገጥ የሁሉም አካላት ተሳትፎ እንደሚያስፈልግ የገለጹት የአገር ሽማግሌው፤ ተቃርኖ ያላቸው ኃይሎች ሕዝቡን ወደ ችግር ውስጥ ከመክተት ውጭ በጦርነት አሸናፊ የሚሆን አካል እንደማይኖር ተናግረዋል። በመሆኑም ማናቸውንም አለመግባባቶች በሰለጠነ መንገድና በውይይት የመፍታት ባህል ሊጎለብት እንደሚገባ ገልጸዋል። መንግሥት የተለያዩ የሀሳብ ነጸብራቆችን በማቀራረብ አካታች የፖለቲካ ምህዳር ለመፍጠር እያደረገ ያለውን ጥረት የጠቀሱት አስተያየት ሰጪው፤ ከጦርነትና ከግጭት የሚገኝ ትርፍ ባለመኖሩ ሁሉም ለሰላም ቅድሚያ ሊሰጥ እንደሚገባ ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ ለተለዋዋጭ ሁኔታዎች የማይበገር አህጉራዊ የጤና ሥርዓት ለመገንባት ሚናዋን አጠናክራ ትቀጥላለች
Jul 8, 2026 784
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):-ኢትዮጵያ ለተለዋዋጭ ሁኔታዎች የማይበገር አህጉራዊ የጤና ሥርዓት ለመገንባት ሚናዋን አጠናክራ እንደምትቀጥል የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ ገለጹ፡፡ "የአፍሪካ የጤና ባለሙያዎችን አቅም ለመጪው ዘመን ማዘጋጀት፦ ትብብርን፣ ቴክኖሎጂን፣ ፈጠራንና አመራርን መጠቀም" በሚል መሪ ቃል በአዲስ አበባ ለሦስት ቀናት ሲካሄድ የነበረው የአፍሪካ የሕክምና ትምህርት ጉባኤ ተጠናቋል።   ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ ያላትን ልምድ እና የካበተ አቅም በመጠቀም የጎረቤት ሀገራት ተማሪዎችን በነጻ በማስተማርና በጤና አገልግሎት ተደራሽነትና ጥራት ያላትን ልምድ ለጉባኤው አካፍላለች። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ በወቅቱ እንደገለጹት፤ ጉባዔው በአህጉሪቱ ለሚያጋጥሙ የጤና ተግዳሮቶች በአፍሪካውያን የሚመራ መፍትሄ ማስቀመጥ ላይ ትኩረት ያደረገ ነው። በጉባኤው ላይ ከበርካታ የአፍሪካ ሀገራት የመጡ የሕክምና ሳይንስ ምሁራን፣ ተመራማሪዎችና ፖሊሲ አውጪዎች የተሳተፉ ሲሆን፣ በጋራ አህጉራዊ ተግዳሮቶችና መፍትሔዎቻቸው ላይ ሰፊ ውይይት መደረጉን ጠቁመዋል። በአህጉሪቱ የሚገኙ የሕክምና ማሰልጠኛ ተቋማት ዘመኑ ከዋጀው የቴክኖሎጂ ዕድገት ጋር እንዲራመዱ እና ብቁ የሰው ኃይል እንዲያፈሩ ለማስቻል ምክክር መደረጉንም አንስተዋል። በጉባኤው ማጠናቀቂያ ላይ የወደፊቱን የጤና ሥርዓት ተግዳሮቶች በብቃት መቋቋም የሚያስችል ጠንካራና ተለዋዋጭ አቅም ለመገንባት የሚያስችል የጋራ አቋም መያዙን አስታውቀዋል። በተጨማሪም የአፍሪካን የጤና ሥርዓት ለማጠናከርና የሥልጠና ጥራትን ለማሻሻል ሰፊ ምክክር ተደርጓል። በዚህም ኢትዮጵያ ለጤናው ዘርፍ የሰው ኃይል ግንባታ የሰጠችውን ልዩ ትኩረት፣ የጎረቤት አገራት ተማሪዎችን በነጻ በማስተማርና የሕክምና መሠረተ ልማት ማስፋፋት ረገድ ያላትን ልምድ በማካፈል አርዓያነት ያለው ተግባር ማከናወኗን ገልጸዋል። በቀጣይም በጉባኤው የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት፣ ኢትዮጵያ ሰው ሠራሽ አስተውሎትን ጨምሮ በቴክኖሎጂ በታገዘ መልኩ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጋር በትብብር እንደምትሠራ ተናግረዋል።   የአፍሪካ የሕክምና ትምህርት ቤቶች ስብስብ ፕሬዚዳንት ፕሮፌሰር ላዮኔል ግሪን ቶምሰን በበኩላቸው፤ በጉባኤው የተቀመጡ አቅጣጫዎች የአህጉሪቱን የጋራ አቅም በማቀናጀት አፍሪካን ከውጭ የሕክምና ጥገኝነት ሙሉ በሙሉ ተላቃ ራሷን እንድትችል ለማድረግ ወሳኝ መሠረት የሚጥሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም