ማህበራዊ
የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት መደጋገፍንና አብሮነትን ይበልጥ በሚያጠናክር መልኩ ይከናወናል
Jul 12, 2025 34
አበሽጌ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፡- የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት መደጋገፍንና አብሮነትን ይበልጥ በሚያጠናክር መልኩ እንደሚከናወን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሀላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር አለምፀሐይ ጳውሎስ ገለጹ። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት እና ተጠሪ ተቋማት በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሃ ግብርን ዛሬ አስጀምረዋል።   በዚህ ወቅት የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሀላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር አለምፀሐይ ጳውሎስ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት መደጋገፍንና አብሮነትን ይበልጥ በሚያጠናክር መልኩ ይከናወናል ብለዋል። በወረዳው ከ33 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የተለያዩ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባራት እንደሚከናወኑም ተናግረዋል። ከሚከናወኑት ተግባራት መካከል 15 የአቅመ ደካማ ወገኖች መኖሪያ ቤቶችና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ እንዲሁም የችግረኛ ቤተሰብ አባላት ለሆኑ ለ2ሺህ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁሶች ድጋፍ እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል።   በተጨማሪም የኮሪደር መንደር እንደሚገነባ ያመለከቱት ሀላፊ ሚኒስትሯ አትክልት እና ፍራፍሬ ልማትን ጨምሮ ሕብረተሰቡን በተለይም ወጣቱን በማሳተፍ የማስፋፋት ስራ እንደሚከናወን ገልጸዋል። በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ በተጀመረው የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሃ ግብር ላይ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት እና ተጠሪ ተቋማት እንዲሁም የጉራጌ ዞን ከፍተኛ አመራሮችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
በክረምት ህክምና በጎ ፈቃድ አገልግሎት ለአምስት ሚሊዮን ዜጎች ነፃ የጤና አገልግሎት ይሰጣል - ዶክተር መቅደስ ዳባ
Jul 12, 2025 33
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በ2017ዓ.ም የክረምት ህክምና በጎ ፈቃድ አገልግሎት ለአምስት ሚሊዮን ዜጎች ነፃ የጤና አገልግሎት እንደሚሰጥ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ አስታወቁ። እስካሁን በተከናወነው የክረምት ህክምና በጎ ፈቃድ አገልግሎት 10 ሚሊዮን ዜጎች የነፃ የጤና አገልግሎት ማግኘታቸውን አመልክተው፤ 12 ሚሊዮን ችግኞች መተከላቸውንም ተናግረዋል። ሀገር አቀፍ ነፃ የክረምት የጤና ምርመራ፣ የምክርና የሕክምና አገልግሎት መርሃ ግብር በአለርት ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ዛሬ ተጀምሯል። በመርሃ ግብሩ ማስጀመሪያ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ፣ የጤና ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የተጠሪ ተቋማትና የጤና ተቋማት አመራር አባላትን ጨምሮ የተለያዩ እንግዶች ተገኝተዋል። ዶክተር መቅደስ ዳባ በመርሃ ግብሩ ላይ እንደገለፁት፤ በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የምርመራና ህክምና ነጻ አገልግሎት ከመስጠት ባሻገር የደም ልገሳ፣ ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ ዜጎች የቤት እድሳትና የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍና የችግኝ ተከላ ይከናወናል። በክረምቱ ወቅት ለአምስት ሚሊዮን ዜጎች ነፃ የህክምና አገልግሎት ለመስጠት የታቀደ መሆኑን ጠቁመው፤ 250ሺህ ችግኞችን መትከል፣ 17 ጤና ተቋማት እድሳት፣ 40 የአቅመ ደካሞች ቤት ግንባታና ለስድስት ሺህ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ እንደሚደረግም ተናግረዋል። ፅዱ የጤና ተቋማት መፍጠር የሚያስችል የፅዳት ዘመቻ፣ የወባ መከላከል ስራና ሌሎች ተግባራት እንደሚከናወኑም ነው የገለጹት። ከ2011ዓ.ም ጀምሮ እስከ 2016 ዓ.ም በተከናወነው የክረምት የህክምና በጎ ፈቃድ አገልግሎት ለ10 ሚሊዮን ዜጎች ነፃ የህክምና አገልግሎት መሰጠቱንና ከ400ሺህ ዩኒት በላይ ደም መሰብሰቡን ተናግረዋል። አምና በተደረገው የክረምት ህክምና በጎ ፈቃድ ከ400 በላይ የተበላሹ የህክምና መሳሪያዎችን በመጠገን ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ ወጪ ማዳን መቻሉን ጠቁመዋል። የአለርት ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ዳይሬክተር ዶክተር ሽመልስ ገዛኸኝ እንዳሉት፤ በ2016 በክረምት በጎ ፈቃድ ሆስፒታሉ ነፃ የጤና ምርመራ፣ የአቅመ ደካማ ቤቶች እድሳት፣ ደም ልገሳና ሌሎች ተግባራትን አከናውኗል። በክረምት በጎ ፈቃድ የተጀመረው መርሃ-ግብር በበጋም ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ ለ2016 ዓ.ም በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ተሳታፊዎች የዕውቅና መርሀ ግብር ተካሂዷል።  
በሐረሪ ክልል ከ40ሺህ በላይ በጎ ፈቃደኞች የሚሳተፉበት የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ይከናወናል - ቢሮው
Jul 12, 2025 39
ሐረር፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል ከ40ሺህ በላይ በጎ ፈቃደኞች የሚሳተፉበት የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት እንደሚከናወን የክልሉ ሴቶች፣ ሕጻናትና ወጣቶች ጉዳይ ቢሮ አስታወቀ። "በጎነት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄደውን ክልላዊ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባር ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። በክልሉ የገጠር እና ከተማ ወረዳዎች በአቅመ ደካማ ቤት እድሳትና ችግኝ ተከላ ሥራ በተጀመረው መርሃ ግብር ላይ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር፣ በብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ጌቱ ወየሳን ጨምሮ ሌሎች የክልሉ አመራሮች ተገኝተዋል። የክልሉ ሴቶች፣ ሕጻናትና ወጣቶች ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ረምዝያ አብዱልዋህብ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ በየዓመቱ በሚከናወነው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የተሳታፊ ወጣቶች ቁጥር እየጨመረ መጥቷል። በተያዘው የክርምት ወራትም በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባራትን ለማከናወን እቅድ ተይዞ ወደ ስራ መገባቱን ነው የተናገሩት። በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራው ከ40ሺህ በላይ በጎ ፈቃደኞች እንደሚሳተፉ ጠቁመው በአገልግሎቱም 14 የትኩረት መስኮች ተለይተው ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያድርጉ የልማት ሥራዎች እንደሚከናወኑ ገልጸዋል። በክልሉ ባለፈው ዓመት በበጎፈቃድ አገልግሎት ከ190 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውንም ወይዘሮ ረምዝያ አመልክተዋል።
በከተማዋ ተገንብተው የተመረቁ መሰረተ ልማቶች አገልግሎቶችን በቅርበት እንድናገኝ ያስችሉናል - ነዋሪዎች
Jul 12, 2025 33
አዳማ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በአዳማ ከተማ ተገንብተው የተመረቁ መሰረተ ልማቶች አገልግሎቶችን በቅርበት ማግኘት እንደሚያስችላቸው የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። የኦሮሚያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ግንባታቸው የተጠናቀቁ መሰረተ ልማቶችን ለአገልግሎት ክፍት ሲያደርግ መቆይቱ ይታወቃል። የአዳማ ከተማ አስተዳደርም የከተማዋን ነዋሪዎች ሁሉን አቀፍ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ መሰረተ ልማቶችን ለአገልግሎት አብቅቷል። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የከተማዋ ነዋሪዎች ሰሞኑን ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት መሰረተ ልማቶች ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ እንቅስቃሴያቸውን በማፋጠን ኑሯቸውን ለመለወጥ የሚያግዟቸው እንደሆኑ ተናግረዋል። ከአዳማ ከተማ የቦሌ ክፍለ ከተማ ጎሮ ወረዳ ነዋሪ ሸሪፍ ኢብራሂም እንደገለፁት ቀደም ባለው ጊዜ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት በአካባቢያቸው ባለመኖሩ እድሜያቸው ለቅድመ መደበኛ ትምህርት የደረሱ ሕጻናት የትምህርት እድል በቅርበት አያገኙም ነበር። ከአካባቢያቸው ራቅ ብሎ በሚገኝ ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ወስዶ ለማስተማርም ከፍተኛ የትራፊክ ፍሰት ያለበት መንገድ ማቋረጥ ግድ ስለሆነ ለደህንነታቸው ስለምንሰጋ ቤት እናውላቸው ነበር ብለዋል። በአሁኑ ወቅት 'ቡኡራ ቦሩ' የተሰኘ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት በአካባቢያቸው መገንባቱ ህጻናት ልጆች የቅድመ መደበኛ ትምህርት ተጠቃሚ መሆን እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። የትምህርት ቤቱ መገንባት የትራንስፖርት ወጪና እንግልትን ያስቀረ ከመሆኑም ባለፈ በቅርበት ትምህርት ቤት በማግኘታቸው ለልጆቻቸው የወደ ፊት እጣ ፈንታም መልካም ሁኔታ የፈጠረ ነው ብለዋል።   በከተማ አስተዳደሩ የተገነቡ የመዝናኛ ማዕከላት በስራ የደከመ አዕምሯችንን ለማዝናናት ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል ያለው ደግሞ የደንበላ ክፍለ ከተማ ነዋሪ ወጣት እዮብ ክንዴ ነው። የመዝናኛ ስፍራዎች በተለይ የከተማው ወጣቶች አልባሌ ቦታ ከመዋል ይልቅ ጊዜያቸውን በጥሩ እና ያማረ ስፍራ እንዲያሳልፉ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል።   ሌላው የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አቶ ለሚ ባለሚ በበኩላቸው አሁን በአካባቢያችን ያማረ መዝናኛ ስፍራ የተሰራበት ቦታ ቆሻሻ የሚጣልበትና ለእይታም የማይማርክ ነበር ይላሉ። ስፍራው የከተማዋ ወጣቶችና አዛውንቶች ጭምር የሚዝናኑበት፣ እረፍት የሚያደረጉበትና የተለያዩ አገልግሎቶች የሚያገኙበት ሆኗል ብለዋል።   በደንበላ ክፍለ ከተማ የወንጂ የወተት ላሞችና የሥጋ ከብቶች ማድለቢያ ማዕከል ውስጥ የመስሪያ ቦታ ተጠቃሚ የሆኑት አርሶ አደር ተስፋዬ ካሳ፣ ከዚህ በፊት የእንስሳት ማድለብ ስራችንን የምናከናውነው በመኖሪያ ቤት ውስጥ ነው ሲሉ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በከተማ አስተዳደሩ የወተት ላሞችና ለስጋ የሚሆኑ በሬዎች የሚያደልቡበት ዘመናዊ ማዕከል በማግኘታቸው መንግስትን አመስግነዋል። የተሻለ የወተት ምርት የሚሰጡ ላሞችን ወደ ማዕከሉ በማስገባት በዘመናዊ መልኩ ለማርባት አቅደን ወደ ስራ ገብተናል ብለዋል። ነዋሪዎቹ በሰጡት አስተያየት ለአገልግሎት ክፍት የሆኑ መሰረተ ልማቶች መሰረታዊ አገልግሎት በቅርበት ማግኘት የሚያስችሏቸው ናቸው።
ኢጋድ የሴቶች የመሬት ባለቤትነትና ውሳኔ ሰጪነት ሚና ለማሳደግ የሚደረጉ ጥረቶችን እንደሚደግፍ ገለጸ
Jul 12, 2025 42
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ሴቶች የመሬት ባለቤትነት መብታቸው እንዲከበር እና በአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄዎች ላይ የመሪነት ሚናቸው እንዲያድግ በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አስታወቀ። ኢጋድ ከሐምሌ 2 ቀን 2017 ዓ.ም አንስቶ በኬንያ ናይሮቢ ስርዓተ ጾታ፣ መሬት እና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም ግንባታ ላይ ሲያካሂድ የቆየው ቀጣናዊ ምክክር ዛሬ ተጠናቋል። በምክክሩ ላይ ሴት የፓርላማ አባላት፣ የፖሊሲ አውጪዎች፣ የሰብዓዊ መብት ተቋማት ተወካዮች፣ የቴክኒክ ባለሙያዎች እና የልማት አጋሮች ተሳትፈዋል። ሁነቱ የስርዓተ ጾታ እኩልነት፣ የመሬት አስተዳደር እና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም ግንባታ ላይ የሚሰሩ ተቋማትን በአንድ መድረክ ያገናኘ ነው። ውይይቱ የመሬት መብቶችን ማስጠበቅ እና ሴቶችን ያሳተፈ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ላይ ሁሉን አቀፍ የፖሊሲ ምክክር ማድረግ እና ቀጣናዊ ትብብርን የማጠናከር ውጥን ያነገበ ነው።   የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ምክትል ዋና ፀሐፊ መሐመድ አብዲ ዋሬ ባደረጉት የማጠቃለያ ንግግር ምክክሩ ሴቶች በመሬት ባለቤትነት እና በአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ የሚያስችል ጠንካራ አቋም የተያዘበት መሆኑን አመልክተዋል። በቀጣናው የሚገኙ ሴቶች ለመሬት ልማት፣ ግብርና እና ለዜጎች ደህነት መጠበቅ ወሳኝ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ቢገኝም በመሬት ባለቤትነት እና ውሳኔ ሰጪነት ላይ ፈተናዎች እያጋጠሟቸው ነው ብለዋል። ሴቶችን ማብቃት ለፍትህ፣ እኩልነት እና ዘላቂ ልማት መረጋገጥ ቁልፍ እንደሆነ ተናግረዋል። የሴት ፓርላማ አባላት ቀጣናዊ ማዕቀፍ እና ቀጣናዊ የፖሊሲ ሰነድ ዝግጅት የውይይቱ ቁልፍ ውጤቶች ናቸው ብለዋል። የአሰራር ማዕቀፎቹ በመሬት መብቶች እና በማይበገር የአየር ንብረት ለውጥ አቅም ላይ ተግባራዊ ምላሽ መስጠት የሚያስችሉ እና የፖለቲካ ቁርጠኝነት የታየባቸው እንደሆነ አብራርተዋል። ሀገራት ቀጣናዊ ማዕቀፎቹን የብሄራዊ እቅዶቻቸው ጋር አጣጥመው እንዲተገብሩና ከቀጣናዊ የአሰራር ስርዓቶች ጋር ስራቸውን እንዲያስተሳስሩ ጥሪ አቅርበዋል። የፓርላማ አባላቱ የለውጥ መሐንዲሶች ናቸው ያሉት ምክትል ዋና ፀሐፊው ሴቶች የመሬት ባለቤት እንዲሆኑና በአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ የመሪነት ሚና እንዲኖራቸው አበክረው እንዲሰሩ ጠይቀዋል። ኢጋድ የሴቶችን የመሬት ባለቤትነት ለማረጋገጥ እና በማይበገር የአየር ንብረት ለውጥ አቅም ግንባታ ያላቸውን ሚና ለማሳደግ ቁርጠኛ እንደሆነ መግለጻቸውን ተቋሙ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ቀጣናዊ ምክክር ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ፣ ጅቡቲ፣ ኬንያ፣ ሶማሊያ፣ ደቡብ ሱዳንና ዩጋንዳ የተካሄዱ ምክክሮች ማጠቃለያ ነው።
በክልሉ የሚያጋጥሙ በሽታዎችን ፈጥኖ በመለየት ምላሽ መስጠት የሚያስችል የጤና ስርዓት የመዘርጋት ስራ ይጠናከራል
Jul 11, 2025 65
ባህርዳር፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በየጊዜው የሚያጋጥሙ በሽታዎችን ፈጥኖ በመለየት ምላሽ መስጠት የሚያስችል የጤና ስርዓት የመዘርጋት ስራ እንደሚጠናከር በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) ገለጹ። በአማራ ክልል ለቀጣይ አምስት ዓመታት የሚተገበር "የጤና ደህንነት ትግበራ /health security activity/" የተሰኘና የህብረተሰቡን ጤንነት የሚያስጠብቅና የሚያሻሽል ፕሮጀክት ዛሬ በባህር ዳር ከተማ ይፋ ተደርጓል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ፣ የክልሉ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት በክልሉ የጤና ስርዓቱን ለማሻሻል የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ ነው። በዛሬው እለት ይፋ የተደረገው ፕሮጀክትም በክልሉ በየጊዜው የሚያጋጥሙ የጤና ችግሮችን ለይቶ መፍታት የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። ፕሮጀክቱ የበሽታ ቅኝት በማድረግ፣ በፍጥነት በመለየትና ለሚመለከተው አካል በማሳወቅ አፋጣኝ መፍትሄ ለመስጠት አጋዥ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል። ፕሮጀክቱ የታለመለትን ግብ እንዲመታ የክልሉ መንግስትና ህዝብ አስፈላጊውን ድጋፍና ትብብር ያደርጋሉ ብለዋል።   የአማራ ክልል የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር በላይ በዛብህ፤ ፕሮጀክቱ በክልሉ በተመረጡ 56 ወረዳዎች የሚተገበር ነው ብለዋል። በክልሉ በጤናው ዘርፍ የሚታዩ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት የቤተ ሙከራ አቅምን ማሳደግና የባለድርሻ አካላትን ተሳትፎ ማጎልበት ላይ በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል።   "የጤና ደህንነት ትግበራ /health security activity/" ፕሮጀክት ምክትል ኃላፊ ዶክተር ኤልያስ ዋለልኝ በበኩላቸው ፕሮጀክቱ የአማራ ክልልን ጨምሮ በአፋርና በትግራይ ክልሎች የሚተገበር መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ፕሮጀክቱ ከሰው ወደ ሰው፣ ከእንስሳት ወደ ሰው፣ ከሰው ወደ እንስሳትና ከአካባቢ ወደ ሰው የሚተላለፉ በሽታዎችን አስቀድሞ በሚካሄድ ቅኝት በመለየት ለመከላከል አልሞ የሚሰራ ነው ብለዋል። በመድረኩ የክልልና የፌደራል የጤናው ዘርፍ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በጌዴኦ ዞን የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ በትብብር እየተሰራ ነው - የዞኑ አስተዳደር
Jul 11, 2025 69
ዲላ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ከህብረተሰቡ እና ከአጋር አካላት ጋር በትብብር የሚደረጉ ጥረቶች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በዞኑ ዲላ ከተማ አስተዳደር በ40 ሚሊዮን ብር ወጪ የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ እየተከናወነ ነው።   ግንባታው የዞኑ አስተዳደር ከዓለም አቀፉ የትምህርትና ባህል ተራድኦ ድርጅት(WECA) ጋር በመተባበር የሚከናወን ሲሆን ግንባታውን በተያዘው ዓመት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚደረግ ተመላክቷል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት በዞኑ የትምህርት ስብራትን በዘላቂነት ለመቅረፍና ጥራትን ለማስጠበቅ ከህብረተሰቡ እና ከአጋር ድርጅቶች ጋር በትብብር እየተሰራ ነው።   በተለይ በተያዘው በጀት ዓመት በዞኑ 80 በመቶ የሚሆኑ ትምህርት ቤቶች ያሉባቸውን የመሰረተ ልማት ችግር በማሻሻል የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ትኩረት እንደሚደረግ ገልጸዋል። የትምህርት ቤቱ ግንባታ በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ ክትትል የሚደረግ መሆኑን አንስተው የትምህርት ጥራትን በማረጋገጥ ሞዴል ትምህርት ቤት ከመፍጠር ባለፈ ደረጃውን ወደ አዳሪ ትምህርት ቤት ለማሳደግ መታቀዱንም ገልጸዋል።   ትምህርት ቤት የእውቀት መገበያያ ብቻ ሳይሆን የትውልዱ የስብዕና ግንባታ ማዕከል መሆኑን ያነሱት ደግሞ የዓለም አቀፉ የትምህርትና ባህል ተራድኦ ድርጅት የቦርድ ሰብሳቢ ባንግ ቱንጋዋን ናቸው። ድርጅታቸው በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች የትምህርት መሰረተ ልማትን በማስፋፋት የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት እያገዘ ነው ብለዋል። በዲላ ከተማ ከዞኑ አስተዳደር ጋር በመተባበር የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከመገንባት ባሻገር በትምህርት ቤቱ የውጭ ቋንቋዎችን በማስተማር የትምህርት ስርዓቱን እየደገፈ መሆኑን ጠቁመዋል።   የጌዴኦ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ ዘማች ክፍሌ በበኩላቸው የትምህርት ቤቱን የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ በተያዘው ዓመት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚደረግ ተናግረዋል። ይህም 13 መማሪያ ክፍሎችን ጨምሮ የአስተዳደርና የመጸዳጃ ህንጻዎችን እንዲሁም የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን ያካተተ ሲሆን ለዚህም ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደሚደረግ ገልፀዋል። በአሁኑ ወቅትም አራት የመጀመሪያ ደረጃ የመማሪያ ክፍሎች ግንባታ መጠናቀቃቸውን አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ በስደተኞች አያያዝ አርዓያነት ያለው ተግባር እያከናወነች ነው
Jul 11, 2025 60
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በስደተኞች አያያዝ አርዓያነት ያለውና የሚደነቅ ተግባር እያከናወነች ነው ሲሉ በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ረዳት ተጠሪ ዴቪድ ካርፕ ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከሃያ ስድስት አገራት በተለያየ ምክንያት የመጡ ከ1 ሚሊዮን በላይ ስደተኞች እና ጥገኝነት ጠያቂዎችን በመቀበል ተገቢውን ጥበቃና ከለላ እየሰጠች ትገኛለች። በኢትዮጵያ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ረዳት ተጠሪ ዴቪድ ካርፕ፥ ኢትዮጵያ የዓለም አቀፍ የስደተኞች አያያዝ መርህን ባከበረ መልኩ ለስደተኞች አገልግሎት እየሰጠች እንደምትገኝ ለኢዜአ ገልጸዋል። ስደተኞች ባሉባቸው አካባቢዎች የመንገድ፣ የውሃ፣ የመብራት፣ የትምህርት፣ የጤና እና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ተገንብተው አገልግሎት እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ስደተኞች ከተቀባዩ የህብረተሰብ ክፍል ጋር በማስተሳሰር በስራ እድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑንም እንዲሁ፡፡ ይህም ኢትዮጵያን ለስደተኞች ከፍተኛ ትኩረት ከሚያደርጉ እና ክብር ከሚሰጡ የዓለም ሀገራት መካከል አንዷ እንደሚያደርጋት አንስተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ በስደተኞች አያያዝ ዙሪያ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት ለሌሎች የዓለም አገራት አርዓያ እንደሚሆኑም ጠቁመዋል፡፡ ረዳት ተጠሪው አክለውም የኢትዮጵያ መንግስትና ህዝብ ለዚህ ተግባራቸው ምስጋና ይገባቸዋል ነው ያሉት፡፡ በቀጣይ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን በስደተኞች አያያዝ ላይ ያለውን ቅንጅታዊ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡  
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከህሊና እርካታ ባለፈ ማኅበራዊ ትስስር እያጎለበተ መጥቷል - አቶ መለስ አለሙ
Jul 11, 2025 59
ሐረር፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከህሊና እርካታ ባለፈ ማኅበራዊ ትስስርን እያጎለበተ መምጣቱን በብልፅግና ፓርቲ የዋና ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለስ ዓለሙ ተናገሩ። በኦሮሚያ ክልል አምስት ሚሊዮን ሴቶች የሚሳተፉበት የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በማያ ከተማ ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በፕሮግራሙ ማስጀመሪያ ላይ የተገኙት በብልፅግና ፓርቲ የዋና ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለስ ዓለሙ እንደገለጹት በዘንድሮው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ሴቶችና ወጣቶች፣ የሲቪክ ማህበራት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ሌሎች የሚሳተፉበት የተለያዩ ተግባራት ይከናወናሉ።   በፕሮግራሙ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላን ጨምሮ የአቅመ ደካማ መኖሪያ ቤቶች እድሳት፣ የድጋፍና እንክብካቤ እንዲሁም ሌሎች ስራዎች ይከናወናሉ ብለዋል። እነዚህ የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች ከህሊና እርካታ ባለፈ ወንድማማችነትንና ማህበራዊ ትስስርን እያጠናከሩ በመምጣታቸው ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የሴቶች ክንፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ሳሚያ አብደላ እንደገለጹት በክልሉ አምስት ሚሊዮን ሴቶች የሚሳተፉበት የክረምት በጎ ፈቃድ ተግባራት ተጀምረዋል።   በመርሃ ግብሩም የአቅመ ደካማ መኖሪያ ቤት እድሳት፣ የደም ልገሳ፣ ማዕድ ማጋራት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላን ጨምሮ 11 የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች እንደሚከናወኑ ገልጸው ይህም ሴቶች እርስ በእርስ እንዲደጋገፉ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። በኦሮሚያ ክልል የማያ ከተማ ምክትል ከንቲባ ታደለ ንጉሴ በበኩላቸው በከተማ መስተዳድሩ በሚከናወነው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ300 ሺህ በላይ በጎ ፈቃደኞች በ34 የክረምት በጎ ፈቃድ ተግባራት እንደሚሳተፉ ጠቁመዋል።   የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራዎች ህብረተሰቡን እየደገፈና የወጣቶችን ተሳትፎና የመረዳዳት ባህልና እሴትን እያጎለበተ መምጣቱን ገልጸዋል። ከታማሚ ልጃቸው ጋር በፈረሰ ቤታቸው ውስጥ ሲኖሩ ለችግር ተጋልጠው እንደነበር ያስታወሱት ደግሞ በማያ ከተማ አስተዳደር የአደሌ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ዙቤዳ ቃሲም ናቸው።   አሁን ላይ ይህን ችግራቸውን የበጎ ፈቃደኞች ተመልክተው ቤታቸው በማደሳቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል። መኖሪያ ቤታቸው ከማርጀቱ የተነሳ ጉዳት እንዳይደርስባቸው ለህይወታቸው ይሰጉ እንደነበር የገለጹት ደግሞ ሌላው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተጠቃሚው አቶ ሸሪፍ ኢብራሂም ናቸው።   ይህን ችግራቸውን በመረዳት የማያ ከተማ መስተዳድርና ነዋሪዎች ቤታቸውን በመገንባታችው መደሰታቸውን ተናግረዋል። በፕሮግራሙ የብልፅግና ፓርቲ ሴቶች ክንፍና ሌሎች የፌደራልና የክልል የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ አመራሮች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ ያሏትን የቱሪዝም ፀጋዎች ለአለም በማስተዋወቅ የዘርፉን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የባለድርሻ አካላት ቅንጅት ያስፈልጋል - የዘርፉ ባለሙያዎች
Jul 11, 2025 64
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡-ኢትዮጵያ ያሏትን የቱሪዝም ፀጋዎች ለአለም በማስተዋወቅ የዘርፉን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው ሊሰሩ እንደሚገባ የዘርፉ ባለሙያዎች ገለፁ። በኢትዮጵያ በአገር በቀል ሪፎርሙ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰሩ ካሉ አምስት የኢኮኖሚ ምሰሶዎች መካከል አንዱ ቱሪዝም ነው። የአዳዲስና ነባር የቱሪዝም መዳረሻዎች ልማት እየተከናወነ ሲሆን ዘርፉ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ የሚያበረክተውን ሚና ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። ይሄንንም በማስመልከት አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የቱሪዝም ባለሙያዎች እንዳሉት መንግስት የሰጠው ትኩረት ለዘርፉ ከፍተኛ መነቃቃትን መፍጠር ችሏል። የታላቁ ኢትዮጵያ አስጎብኚ ድርጅቶች ማህበር አባልና የፕሌዠር ኢትዮጵያ አስጎብኚና የጉዞ ወኪል ባለቤት ናሆም አድማሱ እንዳሉት ኢትዮጵያን በቱሪዝም ዘርፍ የበለጠ ከፍ ማድረግ የሚያስችል አቅም ተፈጥሯል።   ሀገሪቱ ያላትን በርካታ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የመስህብ ቦታዎች በማስተዋወቅና መልካም መስተንግዶን ለጎብኚዎች በመስጠት ከዘርፉ የሚገኘውን ተጠቃሚነት ማሳደግ ያስፈልጋል ብለዋል። የጉዞና ጉብኝት ጋዜጠኛ ሄኖክ ስዩም በበኩሉ በአሁኑ ሰዓት መንግስት ከመቼውም ጊዜ በላይ ለቱሪዝም ዘርፉ ትኩረት ሰጥቶ መስራቱን ተናግሯል።   የቱሪዝም መዳረሻ ልማት ስራዎች በመላው ሀገሪቱ እየተከናወኑ መሆናቸውንና ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት ለቱሪዝም መነቃቃት አስተዋፅኦ እያበረከቱ መሆኑን ተናግሯል። ለቱሪስቶች ምቹ ሁኔታን መፍጠር የሚያስችሉ የቱሪዝም መዳረሻ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የአዲስ አበባ ሆቴልና ቱሪዝም ባለሙያዎች ማህበር ኤክስክዩቲቭ አባል ወንድምዬ አዋሽ ናቸው።   ኢትዮጵያ ያሏትን የቱሪዝም ፀጋዎች ለአለም በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ላይ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል። ጠንካራ የቱሪዝም ዲፕሎማሲ ያላት አገርን ለትውልድ ለማስተላለፍም ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው ሊሰሩ እንደሚገባ ተናግረዋል። የቱሪዝም ዘርፉን ተጠቃሚነትና ዘላቂነት ለማረጋገጥ የዘርፉ ተዋንያን መልካም ስነምግባርን በመላበስ በቅንጅት መስራት ላይ ትኩረት እንዲሰጡም እንዲሁ።
በምዕራብ ወለጋ ዞን በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ10 ሺህ በላይ የአቅመ ደካማ ቤቶች ግንባታና እድሳት ይከናወናል
Jul 11, 2025 60
ጊምቢ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡-በምዕራብ ወለጋ ዞን በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ10 ሺህ በላይ የአቅመ ደካማ ቤቶች ግንባታና እድሳት ለማከናወን ወደ ተግባር መገባቱን የዞኑ ሴቶችና ህፃናት ጉዳዮች ጽህፈት ቤት አስታቀ። በጽህፈት ቤቱ የሴቶች ንቅናቄና ተሳትፎ የማስፋት ቡድን መሪ አቶ ኤፍሬም ጃለታ፣ በዞኑ በዘንድሮ በጎ ፈቃድ አገልግሎት የአረንጓዴ አሻራ፣ የአቅመ ደካሞች ቤት ዕድሳትና ግንባታ፣ የማጠናከሪያ ትምህርት፣ ደም ልገሳ፤ የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍና ሌሎች ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራውን ለማሳካትም ወጣቶችን ጨምሮ ለሁሉም ባለድርሻ አካላት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ ተሰርቷል ብለዋል። የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ለማሳካትም የዞኑ ወጣቶችና ሴቶች አደረጃጀቶችን ጨምሮ አቅም ያላቸው ነዋሪዎች እንደሚሳተፉ ተናግረዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራዎች የበርካታ ሰዎችን ህይወት ከችግር ማውጣት መቻሉን አንስተዋል፡፡ ይህንን በበለጠ በማጠናከር ከ6 ሺህ 489 በላይ ያረጁና 4 ሺህ 326 አዲስ የአቅመ ደካማ ቤቶች ግንባታና እድሳት ለማከናወን ወደ ተግባር መገባቱን አስታውቀዋል። በአጠቃለይ በዚህ ክረምት ወራት በዞኑ በተለያዩ የልማት ዘርፎች በሚከናወን የበጎ ፈቅድ አገልግሎት ይወጣ የነበረን ከፍተኛ የመንግስት ገንዘብ መታደግ ይቻላል ብለዋል። በክረምቱ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራው ከሚሳተፉት መካከል ወጣት ዱላ ቸርነት፤ በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ የተቸገሩ ወገኖችን በማገዝ የዜግነት ግዴታውን ለመወጣት መዘጋጀቱን ገልጿል።   በበጎ ፈቃድ የሚከናወኑ ስራዎች ላይ በመሰማራት ሀገርንና የተቸገሩ ወገኖችን ማገልገል ደስታ የሚሰጥ ተግባር እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡ በዞኑ በየዓመቱ የሚከናወኑ የክረምት ወቅት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራ ሲሳተፍ መቆየቱን የተናገረው ደግሞ የጊምቢ ከተማ ነዋሪ ወጣት አለማየሁ ዳቃ ነው፡፡   በዚህ ክረምትም ከሌሎች ወጣቶች ጋር በመሆን በተለያዩ በጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራዎች ለመሳተፍ መዘጋጀቱን ገልጿል።
መንግሥት በሰቆጣ ቃል ኪዳን እና በትምህርት ምገባ መርሐ ግብር ለትውልድ ግንባታ አመርቂ ስራዎችን እያከናወነ ነው
Jul 11, 2025 56
  አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦መንግሥት በሰቆጣ ቃል ኪዳን እና በትምህርት ምገባ መርሐ ግብር ለትውልድ ግንባታ አመርቂ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን የኢትዮጵያ የትምህርት ቤቶች ምገባ ኢኒሼቲቭ ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬዓለም ሽባባው ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "ከራዕይ ወደ ተግባር፤ የኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ" በሚል መሪ ሀሳብ በኢትዮጵያ ሥርዓተ ምግብ ላይ ያተኮረ ውይይት አካሂዷል፡፡   በዚሁ ወቅት የኢትዮጵያ የትምህርት ቤቶች ምገባ ኢኒሼቲቭ ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬዓለም ሽባባው እንዳሉት፥የኢትዮጵያ መንግስት ትልልቅ ኢኒሼቲቮችን በመቅረፅ ለትውልድ ግንባታ በርካታ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ከዚህም ውስጥ የትምህርት ቤት ምገባ እና የሰቆጣ ቃል ኪዳን ተጠቃሽ መሆናቸውን ያነሱት ዳይሬክተሯ፤ ከቅድመ መደበኛ እስከ 8ኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች የምገባ መርሐ ግብር እያከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ለአብነትም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቀን ሁለት ጊዜ ከ800 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በመመገብ ላይ እንደሚገኙ ጠቁመው፤ ከ13ሺህ በላይ ለሆኑ እናቶችም የስራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል፡፡ የምገባ መርሃ ግብሩ መንግስት የተገበራቸው ትልልቅ ኢኒሼቲቮች ውጤታማ መሆናቸውን አንዱ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የተማሪዎች መጠነ ማቋረጥና ማርፈድ ማስቀረት ማስቻሉን ተናግረዋል፡፡ በሰቆጣ ቃልኪዳን ህጻናት ከጽንስ ጀምሮ ተመጣጣኝ ምግብ እንዲያገኙ በማስቻል የነገዋን ኢትዮጵያ በመገንባት ላይ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡ የሰቆጣ ቃልኪዳን በማስፋፋት ምዕራፍ ትግበራው በ2017 በጀት ዓመት በ334 ወረዳዎች የተተገበረ ሲሆን በዚህም በሚሊዮን የሚቆጠሩ የሚያጠቡና ነፍሰጡር እናቶች እንዲሁም በርካታ ህጻናት ተጠቃሚ መሆናቸው ይታወቃል።
በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ224 ሚሊዮን ብር በላይ ከምዝበራ ማዳን ተችሏል
Jul 11, 2025 52
ቦንጋ ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡- በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተከናወነ ሙስናን የመከላከል ስራ ከ224 ሚሊዮን ብር በላይ የመንግሥትና የህዝብ ሃብት ከምዝበራ ማዳንና ማስመለስ መቻሉን የክልሉ ስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ገለጸ። በበጀት ዓመቱ በክልሉ 4 ሺህ 200 የመንግስት ሰራተኞችን በመመዝገብ የምስክር ወረቀት መሰጠቱም ተገልጿል። የክልሉ ስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሉሰው ዘውዴ ለኢዜአ እንደገለፁት፣ በተገባደደው በጀት ዓመት በትውልድ ስነ-ምግባር ግንባታና የአስቸኳይ ሙስና መከላከል ስራ ትኩረት ተደርጎ ሲሰራ ቆይቷል። እንዲሁም በአሰራር ስርዓት ጥናትና በሙስና መረጃ ማደራጀትና መተንተን እንዲሁም በተቋም ግንባታ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል። በዓመቱ 729 ጥቆማዎችን በጽሁፍ፣ በስልክ፣ በአካልና በተለያዩ የመረጃ መቀበያ አማራጮች መቀበሉን ጠቁመዋል። ጥቆማዎቹም በሀሰተኛ ሰነድ መጠቀም፣ በሰነድ ማጭበርበር፣ በሀብት ምዝበራ፣ ስልጣንን ያለ አግባብ መጠቀም፣ ምንጩ ያልታወቀ ሀብት ማፍራትና በሌሎች ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ እንደነበሩም ኮሚሽነር ሙሉሰው ገልፀዋል። ከቀረቡት ጥቆማዎች ውስጥ 292ቱ በአስቸኳይ ሙስና መከላከል እንዲሁም 124ቱ ላይ ማስረጃን በማደራጀትና በመተንተን ለፍትሕ አካላት የማስተላለፍ ስራ ተሰርቷል ብለዋል። ኮሚሽነሩ አያይዘውም 202 ጥቆማዎች በአስተዳደራዊ እርምጃ ምላሽ የተሰጠ ሲሆን ቀሪ 27 የምክርና የህግ ከለላ መስጠት ተችሏል ነው ያሉት። 292 ጥቆማዎች ላይ በተሰራው አስቸኳይ የሙስና መከላከል ስራ ሊመዘበር የነበረን ከ178 ሚሊዮን 871 ሺህ ብር በላይ ማዳን መቻሉን ኮሚሽነር ሙሉሰው ተናግረዋል። እንደ ኮሚሽነር ሙሉሰው ገለጻ ከገንዘብ በተጨማሪ ከ166 ሺህ 708 ካሬ የከተማ እንዲሁም ከ505 ሄክታር በላይ የገጠር መሬት ማዳን ተችሏል። በኦዲት ግኝት ተመዝብሮ የነበረን ሀብት ለማስመለስ በተደረገው ጥረትም ከ45 ሚሊዮን 618 ሺህ ብር በላይ እንዲሁም በዓይነት የተለያዩ የመንግስት ንብረትና ቁሳቁሶችን የማስመለስ ስራ መሰራቱን ገልፀዋል። ይህም በአጠቃላይ በተሰራው ሙስናን የመከላከል ስራ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ224 ሚሊዮን 489 ሺህ ብር በላይ በገንዘብና በዓይነት የመንግሥትና የህዝብ ሃብትን ከምዝበራ ማዳንና ማስመለስ መቻሉን ነው የገለጹት። በተጨማሪም በተገባደደው በጀት ዓመት 4 ሺህ 200 የመንግስት ሰራተኞችን በመመዝገብ የምስክር ወረቀት መሰጠቱን ጠቁመው የመረጃውን ትክክለኛነት በማረጋገጥ ግልፀኝነትና ተጠያቂነትን የማስፈን ስራ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። የኮሚሽኑን የአሰራር ስርዓት ከማሻሻልና ብቃት ከማሳደግ አኳያ በተሰሩ ስራዎች ሶስት የተለያዩ ሕጎችን በማዘጋጀት ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉን ኮሚሽነሩ አስረድተዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም ተግባራቱን ይበልጥ አጠናክሮ በማስቀጠል የተመዘገቡ ሀብቶችን ትክክለኛነት ማጣራትና የሀብት ምዝገባን በቴክኖሎጂ የማስደገፍ ስራ በትኩረት ይሰራል ብለዋል ።
በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ16 ሺህ በላይ የተለያዩ የታዳሽ ሃይል አማራጮች ለማህበረሰቡ እንዲቀርቡ ተደርጓል
Jul 11, 2025 47
ወልዲያ ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፡- በሰሜን ወሎ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ16 ሺህ በላይ የተለያዩ የታዳሽ ሃይል አማራጮችን በማቅረብ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የዞኑ ውሃና ኢነርጂ መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የአማራጭ ኢነርጂ ቡድን መሪ ወይዘሮ ትርሃስ እቋር ለኢዜአ እንደገለጹት በገጠር ተበታትኖ የሚኖረውን ማህበረሰብ በታዳሽ ሃይል ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ነው። በበጀት ዓመቱ ከ16 ሺህ በላይ የታዳሽ ሃይል አማራጮችን በማቅረብ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ከቀረቡት የሃይል አማራጮች ውስጥም 12 ሺህ 187 የተሻሻሉ ማገዶ ቆጣቢ ምድጃዎች፣ 3 ሺህ 764 የሶላር ቁሳቁሶችና 112 የባዮ ጋዝ ግንባታ መሆናቸውን አስረድተዋል።   በቀረቡት የሃይል አማራጮችም 16 ሺህ 63 እማና አባዎራዎችን ከነሙሉ ቤተሰቦቻቸው ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። የሃይል አማራጮቹን ማቅረብ የተቻለውም ከመንግስትና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች በተገኘ ከ15 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪና በህብረተሰቡ ተሳትፎ መሆኑን አስገንዝበዋል። በመቄት ወረዳ የ017 ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር አስረሴ ቦጋለ እንደገለጹት ከባለሙያዎች በተሰጣቸው ምክር በመታገዝ የባዮ ጋዝ ግንባታ በማካሄድ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህም የምግብ ማብሰል፣ የመብራት አገልግሎት፣ ከባዮ ጋዝ ተረፈ ምርቱ የተፈጥሮ ማዳበሪያና ሌሎች ጥቅሞችን ማግኘታቸውን ተናግረዋል። "የተሻሻለ ፈጣን የምድጃ ተጠቃሚ በመሆናቸው ከኩበትና ከእንጨት ጪስ ስቃይ መገላገላቸውን የገለጹት ደግሞ በዞኑ የላስታ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ እታለም ጎሹ ናቸው። " በማገዶ ፍለጋ ብዙ ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን ያባክኑ እንደነበር ጠቁመው አሁን ላይ ጤናቸውን በጠበቀና ወጪን በቀነሰ መልኩ ምግብ አብስለው ቤተሰባቸውን እየመገቡ መሆኑን ተናግረዋል።
በመዲናዋ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ 15 ሺህ 960 ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቅተዋል
Jul 11, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡- በመዲናዋ በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት 15 ሺህ 960 ፕሮጀክቶች በመንግሥትና በህብረተሰብ ተሳትፎ ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። 3ኛው የአዲስ አበባ ምክር ቤት 4ኛ አመት የስራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ጉባኤ መካሄድ ጀምሯል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ የ2017 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት በማቅረብ ላይ ይገኛሉ። በሪፖርታቸውም በ2017 በጀት ዓመት የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በርካታ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። ከእነዚህም መካከል የአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል፣ የገበያ ማዕከላት፣ የጤና የትምህርት የኪነጥበብ እና ሌሎችም መሰረተ ልማቶች ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። የአቅመ ደካማ ቤቶችን መገንባት እና ማደስ በበጎ ፈቃደኞች ብቻ የተሰራው 8 ሺህ 786 ቤቶች ሲሆን በከተማ አስተዳደሩ በጀት የተገነቡ መኖሪያ ቤቶች ደግሞ 5 ሺህ 176 መኖሪያ ቤቶች ናቸው ብለዋል። በኮሪደር ልማቱም በካዛንችስ፣ ቦሌ፣ ልደታ፣ ላፍቶ፣ አራት ኪሎ እና ሌሎችም በግልና በመንግስት ተሳትፎ 5 ሺህ 563 ሱቆች መጠናቀቃቸውን ያነሱት ከንቲባዋ፥ 1 ሺህ 64 መስሪያ ሼዶችም ወደ አገልግሎት ገብተዋል ነው ያሉት። በቀዳማዊ ልጅነት ንቅናቄም አዲስ አበባ ህጻናትን ለማሳደግ ምቹ ከተማ እንድትሆን በተጀመሩ ተግባራት 1 ሺህ 155 የህጻናት መጫወቻዎች መገንባታቸውን ገልጸዋል። ለወጣቶች ስፖርት ማዘውተሪያ 122 ሜዳዎች ተጠናቀው ወደ አገልግሎት መግባታቸውንም አብራርተዋል። በበጀት ዓመቱ በመጀመሪያው ምዕራፍ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ 153 የመኪና ማቆሚያና ተርሚናሎች ተጠናቀው ወደ አገልግሎት መግባታቸውን ገልጸዋል። ሌሎችም በርካታ የልማት ሥራዎችን ጨምሮ 15 ሺህ 960 ፕሮጀክቶች ተገንብተው ለአገለግሎት መብቃታቸውን በማንሳት ከእነዚህ ውስጥም 16ቱ ሜጋ ፕሮጀክቶች ናቸው ብለዋል። ከዚህም ባለፈ 9 ሺህ የሚሆኑት በህብረተሰብ ተሳትፎ እና በበጎ ፈቃድ አገልግሎት የተሰሩ መሆናቸውን አንስተዋል። የከተማዋን የመንገድ ተደራሽነትና የትራፊክ ፍሰትን የሚያሻሽሉ ጥራት ያላቸው የመንገድ መሰረተ ልማቶችን ለመገንባት በተሰራው ስራም 1 ሺህ 392 ኪሎ ሜትር የአስፋልት፣ የኮብል፣ የጠጠር፣ እና የእግረኛ መንገዶች ግንባታና ጥገና መከናወኑን ጠቅሰዋል።
የክልሉ መንግስት የጤና አገልግሎት ለሕብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ ተጠቃሚነቱን የሚያጎለብት ተግባር እያከናወነ ነው
Jul 10, 2025 92
ቦንጋ ፤ ሐምሌ 3/2017 (ኢዜአ)፡- የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል መንግስት የጤና አገልግሎት ለሕብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ ተጠቃሚነቱን ይበልጥ የሚያጎለብት ተግባር እያከናወነ መሆኑ ተገለጸ። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) በካፋ ዞን የተገነባውን የቆንዳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።   በተጨማሪም በካፋ ዞን ሳይለም ወረዳ ከ78 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው የያዶታ ኮንስትራክሽንና ኢንዱስትሪያል ኮሌጅና የያዶታ ጤና ጣቢያ ቀዶ ጥገና ማዕከልንም መርቀዋል ። በዚህ ወቅት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት፤ የክልሉ መንግስት የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያሳድጉ በርካታ ተግባራት እያከናወነ ነው ። በተለይም ከማህበራዊ ዘርፍ ውስጥ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትንና ጥራቱን ለማሻሻል በተወሰደው እርምጃ የዛሬውን ጨምሮ ባለፉት የለውጥ ዓመታት አራት የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች ተመርቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ ተደርጓል ብለዋል። በተጨማሪም በርካታ የማስፋፊያና በግብአት የማሟላት ስራም መከናወኑን አንስተዋል።   ዛሬ የተመረቀው የቆንዳ ሆስፒታል ለወረዳውና ለአጎራባች አካባቢዎች ነዋሪዎች አገልግሎት የሚሰጥ ነው ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ፤ የክልሉ መንግስት የጤና አገልግሎት ለሕብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ ተጠቃሚነቱን ይበልጥ የማጎልበት ተግባር እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። የክልሉ ጤና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኢብራሂም ተማም በበኩላቸው፤ የቆንዳ የመጀመሪያ ሆስፒታል በክልሉ መንግስት 120 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መገንባቱን ገልጸዋል።   የሆስፒታሉ መገንባት ሕብረተሰቡ የተሻለ የጤና አገልግሎት እንዲያገኝ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል። ዛሬ የተመረቀው የቆንዳ ሆስፒታል በሕብረተሰቡ ሲነሳ ለቆየው ጥያቄ መልስ የሰጠ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ ናቸው ።   በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደርና የግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ማስረሻ በላቸውን ጨምሮ ሌሎችም ከፍተኛ አመራሮችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በክልሉ በጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች የበርካቶችን ሕይወት እየታደጉ ነው
Jul 10, 2025 74
  ወላይታ ሶዶ፤ሐምሌ 3/2017 (ኢዜአ))፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በጎ ፈቃደኛች በተከታታይ እያበረከቱት ያለው የደም ልገሳ የበርካቶችን ሕይወት እየታደጉ መሆኑ ተገለጸ። የክልሉ ጤና ቢሮ የዓለም የደም ለጋሾ ቀንን ምክንያት በማድረግ ለበጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾችና ተቋማት የምስጋና እና የእውቅና መርሃ ግብር ዛሬ በወላይታ ሶዶ ከተማ አካሂዷል። ዕውቅና ከተሰጣቸው በጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች መካከል ወጣት ሄኖክ ኮይራ በአርአያነት ተጠቅሷል። ወጣቱ በአርአያነት የተጠቀሰውም ለ65 ተከታታይ ጊዜ በበጎ ፈቃደኝነት ደም በመለገሱ ሲሆን፤ለዚህም ከክልሉ ጤና ቢሮ የዕውቅናና ምስጋና የምስክር ወረቀት እንዲሁም ሜዳሊያ ተበርክቶለታል። ወጣት ሄኖክ የሚለገሰው ደም በተለያዩ ምክንያቶች ደም የሚያስፈልጋቸውን ሰዎች ሕይወት እየታደገ መሆኑን ሲያስብ እና ሲመለከት የአዕምሮ እርካታ ከመስጠት ባለፈ ደስታ እንደሚሰማው ይናገራል። የክልሉ ጤና ቢሮ ለተከታታይ 65 ጊዜ ደም በመለገሱ የሰጠው እውቅና ልግስናውን ይበልጥ ለማጠናከር የሚያበረታታው መሆኑን ገልጿል። ሌሎችም ወጣቶች የሚተካ ደም በመለገስ የማይተካ የሰው ሕይወት ቢታደጉ በህይወታቸው ይበልጥ ደስተኛ ሊሆኑ እንደሚችሉ አስተያየት ሰጥቷል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ሃላፊ አቶ እንዳሻው ሽብሩ በበኩላቸው፤ ወጣት ሄኖክ ኮይራን ጨምሮ በበጎ ፈቃድ ደም የሚለግሱ አካላት የበርካቶችን ሕይወት እየታደጉ በመሆናቸው ሊመሰገኑ ይገባል ብለዋል።   ቢሮው የሕብረተሰቡን ግንዛቤ ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የለጋሾች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን ተናግረዋል። በበጎ ፈቃድ ደም በመለገስ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ አካላትን ዕውቅና የመስጠት ስራ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ሃላፊው አስታውቀዋል።
በኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግርን ለማሳካት የሁሉም ሚና ወሳኝ ነው
Jul 10, 2025 82
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ዘላቂ እና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግርን ለማሳካት የሁሉም አካላት ሚና ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ፡፡ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "ከራዕይ ወደ ተግባር፤ የኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ" በሚል መሪ ሀሳብ በኢትዮጵያ ሥርዓተ ምግብ ላይ ያደረገ ውይይት ተካሂዷል። በዚሁ ወቅት የመነሻ ጽሁፍ ያቀረቡት የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬው ተገኝ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለዘላቂ የልማት ግቦች ስኬት የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ትገኛለች። ኢትዮጵያ የምግብ ስርዓት ሽግግር ትግበራን በመጀመር ግንባር ቀደም ሀገር መሆኗን ገልጸዋል።   2ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ በኢትዮጵያ እና በጣሊያን አስተናጋጅነት ከሐምሌ 20 እስከ 22 ቀን 2017 በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ገልጸዋል። ጉባዔው በኢትዮጵያ መካሄዱ ለሀገር ገጽታ ግንባታ ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም ኢትዮጵያ ለጀመረችው የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ እውቅና የሚሰጥ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በተለይም ከለውጡ ወዲህ የምግብ ስርዓት ሽግግርን የሚያፋጥኑ የተለያዩ ብሔራዊ ፕሮግራሞችን በመቅረጽ በትኩረት እየሰራች እንደምትገኝ ይታወቃል። ለአብነትም የሌማት ትሩፋት፣ የስንዴ ልማት፣ አረንጓዴ አሻራ፣ የትምህርት ቤት ምገባ፣ ኢትዮጵያ ታምርት እንዲሁም የሰቆጣ ቃል-ኪዳን ኢንሼቲቮች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ የትምህርት ቤቶች ምገባ ኢኒሼቲቭ ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬዓለም ሺባባው በመድረኩ የኢትዮጵያ መንግስት የሰቆጣ ቃልኪዳን እና የተማሪ ምገባ ኢኒሼቲቮችን በመውሰድ ለትውልድ ግንባታ ትልቅ ሥራ እየሰራ መሆኑን አንስተዋል፡፡   በዚህም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ብቻ ከ8 መቶ ሺህ በላይ ተማሪዎች በቀን ሁለት ጊዜ በመመገብ ላይ መሆኑን ተናግረው፤ በሰቆጣ ቃልኪዳንም ለትውልድ ግንባታ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የተፈጥሮ ሳይንስና ስነ ቀመር ኮሌጅ ዲን ቢቂላ ወርቅነህ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ ግብርና ምርታማነት አቅምን ማሳደግ የሁሉም ሚና ነው ብለዋል፡፡   በተለይም የግሉ ሴክተር የሚጠበቅበትን መወጣት እንዳለበት አንስተው ወደ ምግብ ማቀነባበር እንዲሁም እሴትን የመጨመር ስራ መስራት እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡ የኤንቢሲ ቴሌቪዥን ዋና ስራ አስፈጻሚ ብሩክ ከበደ፤ የምግብ ስርዓት እና የምግብ ሉዓላዊነት የመገናኛ ብዙሃን ዋነኛው አጀንዳ ነው ብለዋል፡፡   በተጨማሪም መገናኛ ብዙሃን በሀገራዊ ዋና ዋና ጉዳዮች ዙሪያ በርካታ ስራዎች መስራታቸውን ጠቁመው፤ ለአብነትም የአረንጓዴ አሻራ፣ የሌማት ትሩፋት እንዲሁም በግብርና መካናይዜሽን ዙሪያ በርካታ ስራዎች መሥራታቸውን ጠቁመዋል፡፡ የኒው ላይፋ ቴን ቻሌንጅ ዴቬሎፕመንት ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ሔለን ጥላሁን በበኩላቸው የምግብ ስርዓትን አሻጋሪና አካታች ለማድረግ ወጣቶችን፣ ሴቶችን እና አካል ጉዳተኞችን አሳታፊ ማድረግ እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡   በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት የሚካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የምግብ ስርዓት ጉባዔን በስኬት ለማስተናገድ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ፡፡
የተጀመሩ የሰላምና የልማት ተግባራትን ለማጠናከር በትኩረት እየተሰራ ነው
Jul 10, 2025 75
ገንዳ ውሃ ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ የተጀመሩ የሰላምና የልማት ተግባራትን በማጠናከር የህዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የምዕራብ ጎንደር ዞን አስተዳደር አስታወቀ። በዞኑ ባለፈው በጀት ዓመት የተሰሩ የሰላምና ልማት ስራዎችን የሚገመግምና በቀጣይ ስለሚሰሩ ተግባራት አቅጣጫ የሚያስቀምጥ መድረክ በገንዳ ውኃ ከተማ ተካሄዷል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ እንዳሉት የዞኑን ፀጋ አሟጦ በመጠቀም የህዝቡን የሰላምና ልማትና ስራዎች ተጠቃሚ ለማድረግ በቁርጠኝነት እየተሰራ ነው።   በአካባቢያቸው ያጋጠመን የጸጥታ ችግሮች ከመፍታት ጎን ለጎን ልማትን ለማፋጠንና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት መሰራቱን አውስተዋል። ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን በተካሄደው ጥረትም የዞኑ ህዝብ የነቃ ተሳትፎ አሁን በዞኑ ለሰፈነው ሰላም ሚና መጫወቱንም አስረድተዋል። የዞኑ ትምህርት መምሪያ ኃላፊ ደሳለኝ አያና በበኩላቸው በችግር ውስጥ ሆነው ተማሪዎችን ተቀብለው ያስተማሩ ትምህርት ቤቶችን በማጠናከርና በቀጣይ ያልጀመሩትን ለማስጀመር በቁርጠኝነት ይሰራል ብለዋል።   በዞኑ የትምህርት ገፅታን ለማሻሻልና የትምህርት ጥራትን ለማሳደግ ከህብረተሰብ ተሳትፎና ከአጋር አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝም አብራርተዋል። ባለፈው ዓመት በርካታ የህዝብ ለህዝብ ውይይቶች ተደርገው የህዝቡን ሰላምና ልማት የማረጋገጥ ተግባር መከናወኑን የገለፁት ደግሞ በብልፅግና ፓርቲ የዞኑ ፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ ወይዘሮ ደመቅ አበበው ናቸው። በዞኑ አብዛኞቹ ቀበሌዎች ወደ ሰላም መመለስ መቻላቸውን አስረድተው ሰላምን በዘላቂነት በማፅናት የፀጥታና የልማት ሰራዎች በተጠናከረ ሁኔታ እንደሚሰሩም አመልክተዋል።   የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኃላፊ አየለ አናውጤ (ዶ/ር) እንዳሉት በክረምት ወቅት ከመደበኛ ስራዎች ጎን ለጎን የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ማሳለጥ እንደሚገባ ጠቁመዋል። የዞኑን አንፃራዊ ሰላም ወደ ተሟላ ሰላም ለማሸጋገር የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች መመለስ እንደሚገባም አፅንኦት ሰጥተዋል። ከግምገማ መድረኩ ጎን ለጎንም የደም ልገሳ መርሃ ግብር ተካሄዷል።
ሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ እንዲሳካ ወጣቶች የሚያደርጉትን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ድጋፍ ማጠናከር አለባቸው
Jul 10, 2025 54
አርባ ምንጭ ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ እንዲሳካ ወጣቶች አቅማቸውን በማስተባበር የሚያደርጉትን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ድጋፍ ማጠናከር እንዳለባቸው የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ምክር ቤት ምስረታ ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የወጣቶች ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ወይዘሮ የሺወርቅ አያና እንደገለጹት ወጣቶች ባለራዕይ በመሆን ባላቸው እውቀትና ክህሎት ለሀገር የብልጽግና ጉዞ መሳካት የበኩላቸውን ሊወጡ ይገባል።   ለሀገር ሰላምና ልማት መጠናከር የወጣቶች የነቃ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፣ መንግስት ለወጣቱ የሰጠውን ልዩ ትኩረት በመጠቀም በሁሉም የልማት መስኮች የሚያደርጉትን ተሳትፎና ያላቸውን ተጠቃሚነት ሊያሳድጉ ይገባል ብለዋል። መንግስት የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሲያከናውናቸው የነበሩ ተግባራትን በቀጣይም አጠናክሮ እንደሚቀጥል ወይዘሮ የሺወርቅ ጠቁመዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ምክትልና የወጣቶች ዘርፍ ሃላፊ አቶ ማርቆስ ማቴዎስ በበኩላቸው እንዳሉት ቢሮው የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ ይገኛል። የክልሉ የወጣቶች ምክር ቤት አስፈጻሚ አካላት ምርጫ ብዝሃነትን መሠረት ያደረገ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊ መሆኑንም ገልጸዋል።   ተመራጮች የክልሉን ወጣቶች ወክለው በተለያዩ መድረኮች እንደሚሳተፉ ገልጸው፣ በቀጣይ እንቅስቃሴያቸው ምክንያታዊ በመሆን ለወጣቶች ሁለንተናዊ ድምፅ ሊሆኑ ይገባል ሲሉም አሳስበዋል። የክልሉ ብሎም የሀገሪቱ እድገትና ሰላም በዘላቂነት ተጠናክሮ እንዲቀጥልም ወጣቶች የበኩላቸውን እንዲወጡ አቶ ማርቆስ ጥሪ አቅርበዋል። የክልሉ ወጣቶች ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሆኖ የተመረጠው ወጣት ቲቶ ሐኩቴ በበኩሉ፣ በቀጣይ የወጣቶች ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት እንዲጎለብትና የወጣቱ ጥያቄዎች በሂደት እንዲመለሱ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅርበት እንደሚሰራ ተናግሯል።   የክልሉ ወጣቶች ያላቸውን እውቀትና ጉልበት አቀናጅተው ለክልሉና ለሀገር ልማት በማዋል የበኩላቸውን እንዲወጡም አስገንዝቧል። ዛሬ በተካሄደው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ምክር ቤት ምስረታ ላይ በሥራ አስፈጻሚነት የተመረጡ 15 ወጣቶችም ቃለ መሃላ ፈጽመዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም