ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
የአፍሪካን የጤና ሥርዓት ከጥገኝነት ለማላቀቅ ከቃል ኪዳን የተሻገረ ቁርጠኛ እርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል - ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀስላሴ
Aug 25, 2026 338
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦የአፍሪካን የጤና ሥርዓት ከጥገኝነት ለማላቀቅ ከቃል ኪዳን የተሻገረ ቁርጠኛ የባለቤትነት እርምጃ መውሰድ እንደሚያስፈልግ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀስላሴ ገለጹ። በአምስት የጤና ዘርፍ ምሰሶዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ለአራት ቀናት የሚቆየው 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ጉባኤ በአዲስ አበባ የአድዋ ድል መታሰቢያ መካሄድ ጀምሯል። የመድረኩ ዋና ዋና የጤና ምሰሶዎች ዘላቂ የጤና ፋይናንስና የዲጂታል ጤና ሥርዓት፣ የመጀመሪያ ደረጃ የጤና ክብካቤ፣ እንዲሁም የጤና ባለሙያዎችና የሀገር ውስጥ ምርቶች አቅም ማሳደግ ናቸው። ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀስላሴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በዓለም አቀፍ ተለዋዋጭ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ተግዳሮቶች ምክንያት በዜጎች ጤና ስርዓት ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እያሳደሩ ይገኛሉ። በዚህም አፍሪካ የዜጎቿን የጤና አጠባበቅ ስርዓት በማዘመን በተለዋዋጭ ዓለም አቀፍ ሁኔታ የሚደርስን የጤና ተጋላጭነት በራስ አቀም ምላሽ መስጠት እንዳለባት ተናግረዋል። እነዚህ ተግዳሮቶች አፍሪካ ቀጣናዊ ትብብር ውስጥ የጋራ ድምጿን ለማጠናከርና በጤና ጉዳዮቿ ላይ ሙሉ ባለቤትነትን ለመያዝ ታሪካዊ ዕድል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል። አፍሪካ በግልጽና በደፋር አቅጣጫ የተመሠረተ የተቀናጀ የጋራ ስትራቴጂ እንደሚያስፈልጋት በመጠቆም፤ በጤና ላይ የምታደርገውን የሀገር ውስጥ ኢንቨስትመንት ማሳደግ እንዳለባትም አስታውቀዋል። የአህጉሪቷን የጤና ስርዓት ለማዘመንም ስትራቴጂክ አጋርነት በማጠናከር የጤና ደኅንነት የራስ መድኃኒቶች፣ ክትባቶችና የምርመራ መሣሪያዎች ማምረትን እንደሚጠይቅ ጠቁመዋል። በዓለም ጤና ድርጅትና በአፍሪካ የበሽታ ቁጥጥርና መከላከያ ማዕከል መካከል ተግባራዊ ቅንጅት በማጠናከር በጉባኤው የሚተላለፉ ውሳኔዎችን ከአጀንዳ 2063 ግብ ጋር አቆራኝቶ መተግበር ያስፈልጋል ብለዋል። ኢትዮጵያ ጤናን እንደ ስትራቴጂካዊ ብሔራዊ ኢንቨስትመንት በመቁጠር በራስ አቅም የበሽታ መከላከልና መቆጣጠር አቅሟን ከጊዜ ወደጊዜ እያጎለበተች እንደሚገኝ ገልጸዋል። የጤና ሥርዓቱን ለማሻሻልና ለማስፋት የተከናወኑ ተግባራትም በእናቶች፣ ሕፃናትና ልጆች ላይ የሚከሰትን በሽታ የመከላከልና የመቆጣጠር አቅም ማጎልበቱን ተናግረዋል። የአፍሪካ ቀጣዩ የጤና ምዕራፍ ከጥገኝነት ይልቅ ባለቤትነትን፣ ከመበታተን ይልቅ ውህደትን፣ ከቃል ኪዳን ይልቅ ተግባራዊ እርምጃን የሚያስቀድም መሆን እንዳለበት አመላክተዋል። ኢትዮጵያ ቀጣናዊና አሕጉራዊ የጤና ኢንቨስትመንት አቅምን ለማጎልበት በሚደረገው ጥረት ንቁ ተሳትፎ በማድረግ ቁርጠኛ አቋም እንዳላት አረጋግጠዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከልጆች ኢንቨስትመንት ፈንድ ፋውንዴሽን መስራች ጋር ተወያዩ
Aug 25, 2026 307
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የልጆች ኢንቨስትመንት ፈንድ ፋውንዴሽን መስራች ክሪስን በለነገዋ ጋር በቀጣይ በጋራ በሚሰሩባቸው ስራዎች ዙሪያ መወያየታቸውን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የልጆች ኢንቨስትመንት ፈንድ ፋውንዴሽን (CIFF) መስራች እና የቦርድ ሃላፊ ክሪስ ሆን እና ቡድናቸውን ለነገዋ የሴቶች የተሃድሶና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከልን ማስጎብኘታቸውንም ገልጸዋል። ለነገዋ ጅማሮው በተለያዩ ማህበራዊ ችግር ውስጥ ያሉ ሴት እህቶቻችን ተስፋና እድላቸው እዲለመልም፣ ክብራቸውና ደህንነታቸው ተጠብቆ የተሻለ ሕይወት እንዲመሩ ከልብ በመነጨ ስሜት የተፀነሰ፣ ተፀንሶም ወደ ተግባር የተቀየረ ትልቅ ራዕይን የሰነቀ ስራ ነው ብለዋል። የእነዚህ እህቶቻችንን ህይወት ለመቀየር፣ ለነገዋ የሴቶች የተሃድሶና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከል ከ2016 ዓ.ም ጀምረነው በ5 ዙር በተለያዩ የሙያ ዘርፎች 3 ሺህ 259 ሰልጣኞችን በክህሎት እና በስብዕና ግንባታ አሰልጥነን ወደ ስራ አሰማርተናል ሲለም ገልጸዋል። ዛሬ ሁሉም ተመራቂዎች ክብር ያለው ኑሮ፣ ብሩህ ተስፋን ሰንቀው አዲስ ህይወት መኖር ጀምረዋል ብለዋል። “ከምንሰራቸው ስራዎች ሁሉ ትልቁ ስራ በሰው ላይ የምንሰራው፣ በተለይም በሴቶች ላይ የምንሰራው ነው” የሚለውን የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) መልዕክት የስራችን ማዕከል አድርገን እየፈፀምን እንገኛለን ነው ያሉት። በከተማችን ላይ ከሚታየው ለውጥ ሁሉ የሚልቀው በለነገዋ ሴቶች ላይ እያየን ያለው ለውጥ ነው ሲሉም ገልጸዋል። ለ”ለነገዋ የተሃድሶና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከል” የሰነቅነው ራዕይ፣ በዓመት እስከ 10 ሺህ ሴቶችን የሚያበቃ፣ እንዲሁም አካታች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ በኢትዮጵያ ብሎም በአፍሪካ ልምድ የሚቀሰምበት የልህቀት ማዕከል እንዲሆን ማስቻል መሆኑንም ጠቅሰዋል። ይህ ራዕይ በተሟላ ሁኔታ እንዲተገበር ሊደግፋን የመጡት የልጆች ኢንቨስትመንት ፈንድ ፋውንዴሽን (CIFF) መስራች ክሪስን በለነገዋ የሴቶች የተሃድሶና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከል የምንሰራቸው ሰው ተኮር ስራዎች አስጎብኝተን በቀጣይም በጋራ በምንሰራቸው ስራዎች ዙሪያ ተወያይተናል ብለዋል።
የአፍሪካ ሀገራት የጤና ተደራሽነትና ዘላቂነትን የሚያረጋግጡ አቅሞችን መገንባት ይጠበቅባቸዋል - መሐሙድ አሊ ዩሱፍ
Aug 25, 2026 304
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ አባል ሀገራት የዜጎቻቸውን የጤና አገልግሎት ተደራሽነትና ዘላቂነት የሚያረጋግጡ አቅሞችን መገንባት እንደሚጠበቅባቸው የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። በአምስት የጤና ዘርፍ ምሰሶዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ለአራት ቀናት የሚቆየው 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ጉባኤ በአዲስ አበባ የአድዋ ድል መታሰቢያ መካሄድ ጀምሯል። የመድረኩ ዋና ዋና የጤና ምሰሶዎችም ዘላቂ የጤና ፋይናንስና የዲጂታል ጤና ሥርዓት፣ የመጀመሪያ ደረጃ የጤና ክብካቤ፣ እንዲሁም የጤና ባለሙያዎችና የሀገር ውስጥ ምርቶች አቅም ማሳደግ ናቸው። በዚሁ ወቅት የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀስላሴ ጨምሮ የአፍሪካ አባል ሀገራት መንግሥታት ከፍተኛ ሥራ ኃላፊዎች፣ የልማት አጋሮች እንዲሁም ቀጣናዊና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች የሥራ መሪዎች ታድመዋል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በዚሁ አጋጣሚ እንዳሉት፤ ሁሉንም አማራጮች በመጠቀም የአህጉሪቱን የጤና ሉዓላዊነት ማረጋገጥ ቀጣይነት ያለው ተግባር ይጠይቃል። የአፍሪካን ጤና ሥርዓት ዘላቂነት በአስተማማኝ መሠረት ለመገንባት የፋይናንስ አቅምን በማጎልበት የምርምርና ፈጠራ አቅሞችን ማሳደግ እንደሚገባም አመላክተዋል። የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት ጉባኤ ጭብጥ አፍሪካውያንን የጤና አገልግሎት ተደራሽነት ለማሻሻል በውሃና ንፅህና አጠባበቅ ላይ ትኩረት ማድረጉን ገልጸዋል። የአህጉሪቱ አባል ሀገራትም የዜጎቻቸውን የጤና ሥርዓት የሚያሻሽሉ የፋይናንስ፣ የሰው ኃይልና የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በራስ አቅም ማቋቋም ባህል ማዳበር እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን የአህጉሪቱን የጤና ሥርዓት ለማሻሻል ከአባል ሀገራት፣ የልማት አጋሮችና ዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይም ከዓለም ጤና ድርጅትና ከልማት አጋሮች ጋር በመተባበር የአህጉሪቱን የጤና ሥርዓቶች በተቀናጀ ዕቅድ ለመምራት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በጉባኤው የሚደረጉ ውይይቶችና የሚወሰኑ ውሳኔዎች ለአፍሪካ የጤና ሉዓላዊነት፣ ራስን መቻልና ዘላቂ የጤና ሥርዓት ግንባታ ጉልህ ሚና እንደሚኖራቸው ጠቁመዋል።
በዞኑ የትምህርት ጥራትንና ተሳትፎን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል
Aug 25, 2026 147
ገንዳ ውኃ፣ ነሐሴ19/2018 (ኢዜአ):- በምዕራብ ጎንደር ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የትምህርት ጥራትንና ተሳትፎን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። የዞኑ ትምህርት መምሪያ በበኩሉ በትምህርት ዘመኑ ከ152 ሺህ በላይ ተማሪዎችን መዝግቦ ለማስተማር ዝግጅት መጠናቀቁን ገልጿል። በዞኑ የተጠናቀቀው የበጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ግምገማና የ2019 ዓ.ም የትምህርት ዘመን የተማሪ ምዝገባ ንቅናቄ መድረክ በዛሬው ዕለት በገንዳ ውኃ ከተማ ተካሄዷል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የትምህርት ጥራትንና ተሳትፎን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል። የተገኙ ተሞክሮዎችን በመቀመርና ችግሮችን በማረም በአዲሱ የትምህርት ዘመን የሚመዘገቡ ተማሪዎችን ሙሉ በሙሉ መዝግቦ ለማስተማር ዝግጅት መደረጉንም ገልጸዋል። በዞን፣ በወረዳና በከተማ አስተዳደር ደረጃ ያለው አመራርም ለትምህርት ምዝገባ ሥራው ልዩ ትኩረት በመስጠት የተያዘውን ግብ ለማሳካት መረባረብ እንዳለበትም አሳስበዋል። የዞኑ ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ደሳለኝ አያና በበኩላቸው፤ በዞኑ በአዲሱ የትምህርት ዘመን ከ152 ሺህ በላይ ተማሪዎችን መዝግቦ ለማስተማር ወደ ሥራ ተገብቷል ብለዋል። በተጀመረው የሙከራ ምዝገባ በሰባት ቅድመ-አንደኛ ደረጃ እና በዘጠኝ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ዕቅዱን 100 በመቶ ማሳካት መቻሉን አስረድተዋል። ይህም ተማሪዎችን በወቅቱ ትምህርት በማስጀመር የትምህርት ተደራሽነትን፣ ጥራትንና አግባብነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። በክረምት ወራቱም የትምህርት ቤቶች ጥገናን፣ መሠረተ ልማትን ማሟላትና ውብና ማራኪ ማድረግን የመሳሰሉ ተግባራትን በማከናወን የተሳካ የትምህርት አጀማመር እንዲኖር እየተሠራ መሆኑንም አክለዋል። የቀጣይ ትውልድ ግንባታ መሠረት የሆነውን ትምህርት ለማጠናከር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የዞኑ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ እንዳለ ማሩ ናቸው። በዚህም ባለድርሻ አካላት የትምህርት ቤቶችን የመሠረተ ልማትና የግብዓት እጥረቶች ለመቅረፍ እንዲሁም አንድም ተማሪ ከትምህርት ገበታ ውጭ እንዳይቀር የማድረግ ተግባርን በኃላፊነት ሊተገብሩ እንደሚገባም አሳስበዋል። በዞኑ የተማሪዎች ምዝገባን እስከ ነሐሴ 30 ቀን 2018 ዓ.ም በማጠናቀቅ ትምህርትን በወቅቱ ለማስጀመር እየተሠራ መሆኑም ተመልክቷል። በመድረኩም የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች፣ የትምህርት ቤተሰቦች፣ ርዕሳነ መምህራን፣ ሱፐርቫይዘሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ውጤት ከዛሬ ምሽት 1፡00 ሰዓት ጀምሮ ይፋ ይሆናል
Aug 25, 2026 2921
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ውጤት ከዛሬ ምሽት 1፡00 ሰዓት ጀምሮ ማየት እንደሚቻል የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት ገለጸ። የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት የ2018 ትምህርት ዘመን የ12ኛ ክፍል ማጠናቀቂያ ፈተና ውጤት የሚገለጽባቸውን የድረ-ገጽ፣ የቴሌግራምና አጭር የጽሑፍ መልዕክት አድራሻዎችንም ይፋ አድርጓል። በዚህም ተፈታኞች ከዛሬ ከምሽት 1፡00 ሰዓት ጀምረው የሚከተሉትን አማራጭ ማስፈንጠሪያዎች (Link) በመጠቀም ውጤታቸውን ማየት የሚችሉ መሆኑን አገልግሎቱ አስታውቋል። ውጤት የሚገለጽባቸው ማስፈንጠሪያዎች፡- በድረ ገጽ ፡ https://result.eaes.et ቴሌግራም፡ https://result.eaes.et/telegram አጭር የጽሑፍ መልዕክት፡ https://result.eaes.et/sms
ሙስሊሙ ማህበረሰብ በዓሉን ሲያከብር ከሐይማኖቱ አስተምህሮ በመነሳት ለሰላምና ልማት የድርሻውን በመወጣት ሊሆን ይገባል
Aug 25, 2026 85
ድሬደዋ፣ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፡-ሙስሊሙ ማህበረሰብ በዓሉን ሲያከብር ከሐይማኖቱ አስተምህሮ በመነሳት ለሰላምና ልማት የድርሻውን በመወጣት ሊሆን እንደሚገባ ተገለጸ። በድሬዳዋ 1 ሺህ 501ኛው የነቢዩ መሐመድ የልደት በዓል (መውሊድ) በደመቀ ሁኔታ ተከብሯል። በድሬደዋ ሁለገብ የወጣቶች ማዕከል በተከበረው በዓል ላይ የነቢዩ መሐመድን አስተምህሮ መሠረት ያደረጉ ትምህርቶችና ውይይቶች ተካሄደዋል። በውይይቱ ላይ የተገኙት የድሬደዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ በወቅቱ እንዳሉት፤ የነቢዩ መሐመድ የልደት በዓል የአንድነት፣ የመደጋገፍ፣ የሰላምና የፍቅር በዓል ነው። ሙስሊሙ ማህበረሰብ በዓሉን ሲያከብር ከሐይማኖቱ አስተምህሮ በመነሳትና የተማረውን በመተግበር ለሀገሪቱ ዘላቂ ሰላምና ልማት የድርሻውን በመወጣት ሊሆን ይገባል ብለዋል። በተለይም እንደ ሀገር የተጀመረውን የሀገረ መንግሥት ግንባታና ችግሮችን በውይይትና በመነጋገር የመፍታት ባህልን በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የድሬደዋ አስተዳደር የእስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ዋና ጸሐፊ ሼህ ከድር አሊ በበኩላቸው፤ ሙስሊሙ ማኅበረሰብ የነቢዩ መሐመድ የመውሊድ በዓልን የሚያከብረው አንድነትን፣ ሰላምንና ፍቅርን በሚያጠናክሩ ተግባራት መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በዓሉ የአንድነት፣ የመረዳዳት፣ የመደጋገፍ፣ የፍቅርና ዘላቂ ሕብረት የሚጠናከርበት መሆኑን ገልጸዋል። ሙስሊሙ ማኅበረሰብ ለሀገርና ለድሬዳዋ ሁለንተናዊ ሰላም፣ ልማትና እድገት እያበረከተ የሚገኘውን አስተዋጽኦ አጠናክሮ እንዲቀጥልም አስገንዘበዋል። በበዓሉ ላይ ከተገኙት ምዕመናን መካከል ወይዘሮ ሰብረን ኢምራን፣ የነቢዩ መሐመድ የመውሊድ በዓል የሚከበረው በድሬደዋ የሚገኙ ችግረኞችን በመደገፍና በመርዳት እንደሆነ ተናግረዋል። ወጣት አባስ አብደላ እና ወጣት አስማ ረፊቅ በበኩላቸው፣ በዓሉ ወጣቶች የእርስ በርስ ፍቅርና አንድነትን የሚያጠናክሩበት መሆኑን ገልጸዋል። ወጣቶቹ አክለውም ለሀገር እድገትና ለአካባቢያቸው ዘላቂ ሰላም እየተወጡ የሚገኙትን ኃላፊነት አጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል።
የመውሊድ በዓልን ያለንን በማካፈልና አቅመ ደካሞችን በመደገፍ እያከበርን እንገኛለን - የዕምነቱ ተከታዮች
Aug 25, 2026 96
ሀዋሳ ፤ነሀሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የመውሊድ በዓልን ያለንን በማካፈልና አቅመ ደካሞችን በመደገፍ እያከበርን ነው ሲሉ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የሀዋሳ ከተማ የእስልምና እምነት ተከታዮች ተናገሩ። 1 ሺህ 501 ኛው የነቢዩ መሐመድ ልደት የመውሊድ በዓል በሀዋሳ ከተማ በተለያዩ ሀይማኖታዊ ኩነቶች እየተከበረ ነው፡፡ ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የእስልምና እምነት ተከታዮች እንደገለፁት፤ የመውሊድ በዓልን ያለንን በማካፈልና አቅመ ደካሞችን በመደገፍ እያከበርን እንገኛለን፡፡ ወይዘሮ ፋጤ ናሥር የከተማው ነዋሪ ሲሆኑ በራህማ መስጂድ በመገኘት ማዕድ በማጋራትና ሌሎች ሐይማኖታዊ ትውፊቶችን በመፈፀም እያከበሩ እንደሚገኙ ገልፀዋል፡፡ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ከሚያከብሩት ባልተናነሰ በመስጂድ በመገኘት ከሌሎች ጋር በጋራ በመሆንና ያላቸውን በማካፈል የሚያሳልፉት የበዓል አከባበር እንደሚያስደስታቸው ገልፀዋል። ወጣት ሀምዛ ከድር በበኩሉ በዓሉን ከሌሎች ወጣቶች ጋር በመሆን አቅመ ደካሞችን በመደገፍና ማዕድ በማጋራት እንዲሁም የበጎ ተግባር መርሀ ግብሮችን በማስተባበር እያሳለፈ መሆኑን አስረድቷል። መደጋገፍና በአብሮነት በዓልን ማሳለፍ ከአባቶቻችን የወረስነው ነው ያለው ወጣት ሀምዛ ይህም ተጠናክሮ እንዲቀጥል እንሰራለን ብሏል። የመውሊድ በዓል ከሌሎች በዓላት በተለየ መልኩ በመስጂድ በመሰባሰብ በአንድ ላይ የምናከብረው በመሆኑ ልዩ ድባብና ድምቀት አለው ያለችው ደግሞ ወጣት ሀያት ኢድሪስ ናት። አክላም የአብሮነትና የመረዳዳት እሴቶቻችንን አጠናክረን ማስቀጠል ላይ ኃላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል ብላለች። በሀዋሳ ከተማ የሐይማኖት መምህር የሆኑት ሀጂ አብዱልፈታ ያሲን በበኩላቸው በእርስ በእርስ መተሳሰብ፣ ያለው ለሌለው በማካፈል እና ከሁሉም ጋር በአብሮነት መኖር የነቢዩ መሐመድ የአስተምህሮ መንገድ ነው ብለዋል፡፡ እኛም አስተምህሮውን ተከትለን ያለንን በማካፈልና በዓሉን በጋራ በማክበር ሐይማኖታችን የሚያዘንን እየፈፀምን እንገኛለን ነው ያሉት፡፡ የነቢዩ የመተሳሰብና የሠላም አስተምህሮ በአንድነት ተከባብሮ ለመኖር የሚያበረክተው አስተዋፅዖ የጎላ ነው ያሉት ሀጂ አብዱልፈታ ይህንኑ ለልጆቻችን ለማስተላለፍ የማስተማር ሥራ እየሰራን ነው ብለዋል፡፡
የመውሊድ በዓልን ፍቅርን፣ ሰላምንና አንድነትን በሚያጠናክር መልኩ እያከበርን ነው- የእምነቱ ተከታዮች
Aug 25, 2026 86
ወልቂጤ ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦የመውሊድ በዓልን ፍቅርን፣ ሰላምንና አንድነትን በሚያጠናክር መልኩ እያከበሩ መሆኑን በወልቂጤ የእምነቱ ተከታዮች ገለጹ። የ1501ኛው የመውሊድ በዓል በወልቂጤ ከተማ በተለያዩ ሃይማኖታዊ እና አብሮነትን በሚያጠናክሩ ሥነ ሥርዓቶች በመከበር ላይ ይገኛል። የወልቂጤ ከተማ የእምነቱ ተከታዮች የመውሊድ በዓልን ፍቅርን፣ ሰላምንና አንድነትን በሚያጠናክር መልኩ እያከበሩ መሆኑን ለኢዜአ ገልጸዋል። ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል አቶ ሳላህዲን ሚፍታ፤ "የመውሊድ በዓል የፍቅር፣ የሰላም እና የአንድነት መገለጫ በመሆኑ በአብሮነትና በመደጋገፍ በደስታ እያከበርነው ነው" ብለዋል። በአብሮነት የመኖር እሴቶችን በተግባር ለማሳየት በዓሉን ከቤተሰቦቻቸውና ከጎረቤቶቻቸው ጋር በጋራ ተሰባስበው እያከበሩ መሆኑንም ተናግረዋል። አቶ ሲራጅ ጀማል በበኩላቸው ነቢዩ መሐመድ ለሰው ልጆች ያሳዩትን የመተዛዘንና የመረዳዳት እሴት በመከተል ትስስርን በሚያጠናክር መልኩ በዓሉን እያከበሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በዓሉን ምክንያት በማድረግ የአካባቢያቸው ነዋሪዎችን በማስተባበር ሕፃናት እና አቅመ ደካማ ወገኖች የደስታው ተካፋይ እንዲሆኑ የማድረግ ሥራ እየሠሩ መሆኑንም ጠቁመዋል። የመውሊድ በዓልን ሃይማኖታዊ አስተምህሮውን በጠበቀ መልኩ በድምቀት እያከበሩ እንደሚገኙ የተናገረው ደግሞ ሌላው የበዓሉ ታዳሚ ወጣት ጠሃ ሳኒ ነው። በዓሉን ያላቸውን በማካፈል፣ በመረዳዳትና አንድነትን በማጠናከር የነቢዩ መሐመድን መልካም ተግባራት በማስታወስ እያከበሩት እንደሚገኙም አመልክቷል። በዛሬው ዕለትም የፍቅርና የአንድነት እሴቶችን በሚያጠናክር መልኩ በዓሉን እያከበሩ መሆናቸውን የጠቆመው ሌላው አስተያየት ሰጪ ረፊቅ ሙሳ፤ በዓሉ የአብሮነት እሴትን ለማጎልበት ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለውም አመልክቷል። በወልቂጤ ከተማ የነቢዩ መሐመድ የልደት በዓል በዱዓ፣ በመንዙማና በማዕድ ማጋራት መርሃ ግብሮች በድምቀት እየተከበረ ይገኛል።
የመውሊድ በዓልን በአብሮነትና የተቸገሩትን በመርዳት እያከበርን ነው - የእምነቱ ተከታዮች
Aug 25, 2026 107
ሳውላ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ) ፡-የመውሊድ በዓልን በአብሮነትና የተቸገሩትን በመርዳት እያከበሩ መሆኑን በጎፋ ዞን ሳውላ ከተማ የእስልምና ሀይማኖት ተከታዮች ገለጹ። 1ሺህ 501ኛው የመውሊድ በዓል በሳውላ ከተማ በተለያዩ ሀይማኖታዊ ስርአቶች እየተከበረ ይገኛል። ከሀይማኖቱ ተከታዮች መካከል ሼህ መሐመድ ዳውድ ለኢዜአ እንደገለጹት በዓሉን የነቢዩ መሐመድ አስተምህሮን በመከተል እያከበሩ ነው። በዓሉን በመተሳሰብ፣ የተቸገሩ ወገኖቹን በመርዳትና ለሀገር ሰላምና አንድነት በመፀለይ እያከበሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ነብዩ መሐመድ ያስተማሩትን ሰላም፣ ፍቅርና አንድነትን በማስተማርና አርዓያ በመሆን ማክበር እንደሚገባም አመልክተዋል። በአሉን በአብሮነትና የተቸገሩትን በመርዳት በደስታ እያከበርን ነው ያሉት ደግሞ የሳውላ ከተማ ነዋሪ አቶ መሐመድ ሲራጅ ናቸዉ። በዓሉን ህሙማንን በመጠየቅና አቅም የሌላቸውን ወገኖች በመርዳት እያከበርን እንገኛለን ብለዋል። አቶ አህመድ ሐሰን በበኩላቸዉ የመውሊድ በዓልን የነቢዩ መሐመድ አስተምህሮን በመከተል በአብሮነት፣ በፍቅርና በሰላም እያከበሩ መሆናቸውን ተናግረዋል ።
በአፍሪካ የጤና ሥርዓትን ለማዘመን የሀገራትን ስትራቴጂካዊ ትብብር ማጠናከር ወሳኝ ነው
Aug 25, 2026 283
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ በአፍሪካ የጤና ሥርዓትን ለማዘመን በሚደረገው ጥረት የሀገራትን ስትራቴጂካዊ ትብብር የበለጠ ማጠናከር ወሳኝ መሆኑን የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀስላሴ ገለጹ። 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባኤ በዓድዋ ድል መታሰቢያ እየተካሄደ ይገኛል። የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀስላሴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት በዓለም አቀፍ ተለዋዋጭ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ተግዳሮቶች ምክንያት በዜጎች ጤና ስርዓት ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ እያሳደሩ ይገኛሉ። በዚህም አፍሪካ የዜጎቿን የጤና አጠባበቅ ስርዓት በማዘመን በተለዋዋጭ ዓለም አቀፍ ሁኔታ የሚደርስን የጤና ተጋላጭነት በራስ አቅም ምላሽ መስጠት እንዳለባት ተናግረዋል። እነዚህ ተግዳሮቶች አፍሪካ ቀጣናዊ ትብብር ውስጥ የጋራ ድምጿን ለማጠናከርና በጤና ጉዳዮቿ ላይ ሙሉ ባለቤትነትን ለመያዝ ታሪካዊ ዕድል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል። አፍሪካ በግልጽና በደፋር አቅጣጫ የተመሠረተ፣ የተቀናጀ የጋራ ስትራቴጂ እንደሚያስፈልጋት ጠቁመው፤ በጤና ላይ የምታደርገውን የሀገር ውስጥ ኢንቨስትመንት ማሳደግ እንዳለባትም አስታውቀዋል። የአህጉሪቷን የጤና ስርዓት ለማዘመንም ስትራቴጂክ አጋርነት በማጠናከር የጤና ደኅንነት የራስ መድኃኒቶች፣ ክትባቶችና የምርመራ መሣሪያዎችን ማምረትን እንደሚጠይቅ ጠቁመዋል። በዓለም ጤና ድርጅት እና በአፍሪካ የበሽታ ቁጥጥርና መከላከያ ማዕከል መካከል ተግባራዊ ቅንጅት ማጠናከር ይገባል ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ በጉባኤው የሚተላለፉ ውሳኔዎችን ከአፍሪካ አጀንዳ 2063 ግብ ጋር አቆራኝቶ መተግበር ያስፈልጋል ብለዋል። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ ጤናን እንደ ስትራቴጂካዊ ብሔራዊ ኢንቨስትመንት እንደምትመለከት ገልጸው፤ ለጤና የሚመደበው በጀት በተከታታይ እየጨመረ መምጣቱንም ተናግረዋል። በመሠረታዊ የጤና አገልግሎት ላይ የተደረገው ኢንቨስትመንት የጤና አገልግሎቶችን ወደ ማኅበረሰቡ ተደራሽ በማድረግ ሚሊዮኖችን የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አንስተዋል። በተጨማሪም የጤና ባለሙያዎችን ቁጥር በማሳደግ የጤና ሥርዓቱን ማጠናከሯን ጠቁመው፤ ይህም በእናቶች፣ ሕፃናት እና ልጆች የመኖር ዕድል ላይ ጉልህ መሻሻል እንዲመጣ ማድረጉን ጠቁመዋል። በአየር ንብረት ለውጥ የሚመጡ የጤና ስጋቶችን ለመቋቋምም ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብሯን በማስፋት ሚሊዮኖችን በማሳተፍ በርካታ ችግኞችን መትከሏን ተናግረዋል። በአዲስ አበባ እየተከናወነ ያለው የልማት ተግባራት ንጹሕ፣ ጤናማና ለነዋሪዎች የተሻለ የከተማ አካባቢን በመፍጠር የሕዝቡን ጤና እና የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። ዘላቂ የጤና ሥርዓት ያለ ሰላምና መረጋጋት ሊኖር እንደማይችል ገልጸው ባለፈው እሁድ ኢትዮጵያ ከተለያዩ የፖለቲካ አመለካከቶች የተውጣጡ ከ4 ሺህ በላይ ተመካካሪዎች የተሳተፉበትን አካታች ብሔራዊ ምክክር በማካሄድ ትልቅ ምዕራፍ አሳልፋለች ብለዋል። ኢትዮጵያም በብሔራዊ ኢንቨስትመንት፣ በቀጣናዊ ትብብርና ለአህጉራዊ ተቋማት በማይናወጥ ድጋፍ የራሷን ድርሻ ለመወጣት ሙሉ ዝግጁ መሆኗን አረጋግጠዋል።
የመውሊድ በዓል እሴቶችን የሕይወታችን መርህ አድርገናል - በጂንካ ከተማ የበዓሉ ታዳሚዎች
Aug 25, 2026 255
ጂንካ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)--የነብዩ ሙሐመድ የልደት በዓል (መውሊድ) የበጎ አርአያነት ምሳሌ በመሆኑ የበዓሉን አሴቶች የሕይወታችን መርህ አድርገናል ሲሉ በጂንካ ከተማ የበዓሉ ታዳሚዎች ገለጹ። 1ሺህ 501ኛው የነብዩ ሙሐመድ የልደት በዓል (መውሊድ) በጂንካ ከተማ ተከብሯል። በክብረ በዓሉ የታደሙት የጂንካ ነዋሪዎች የመውሊድ በዓል የበጎነት ምሳሌ በመሆኑ የበዓሉ አስተምህሮ የሆኑትን አብሮነት፣ ፍቅር እና አንድነት የሕይወታቸው መርህ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል አቶ ዳውድ ሙሐመድ የመውሊድ በዓል የበጎ አርአያነት ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው፣ በዓሉ የነብዩ ሙሐመድን የፍቅርና የርህራሔ አስተምህሮ ለትውልዱ የምናስተምርበት ነው ብለዋል። በዓሉ ሲከበር ፍቅር፣ ርህራሔ፣ ለጋስነት እና አብሮነት ጎልቶ የሚወጣበት በመሆኑ አርአያናቱ የላቀ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛዋ የበዓሉ ታዳሚ ሳውዳ አብዲ በበኩሏ የመውሊድ በዓል በጎነት የሚጎላበት የእዝነት በዓል ነው ብላለች። ለትውልዱ በጎ ምግባርን በማስተማር፣ የተራበን በማብላት፣ የተጠማን በማጠጣት፣ የታረዘን በማልበስ እና ስለ ሀገር ሰላም፣ ፍቅርና አንድነት በጋራ በመፀለይ በዓሉን ማክበራቸውንም ተናግራለች። የመውሊድ በዓል ከሃይማኖታዊ ሥነ-ሥርዓቱ ባሻገር ማኅበራዊ ትስስርና እርስ በርስ የመደጋገፍ እሴትን ስለሚያጠናክር ባህላዊ እሴቶቹን የህይወቷ መርህ ማድረጓን ተናግራለች። በዓሉ የህብረተሰቡን አብሮነት የሚያጠናክሩ የተለያዩ ሰብአዊ ተግባራት የሚከናወኑበት መሆኑ ያነሱት ደግሞ ሌላው የበዓሉ ታዳሚ ሸረፈዲን አብራር ናቸው። የነብዩ መሐመድ የልደት በዓል ያሉትን የአንድነት፣ የፍቅርና የለጋስነት አስተምህሮ በመከተል በዓሉን በአብሮነትና በመተሳሳብ እያከበሩት መሆናቸውን ገልጸዋል። በዚህም በአካባቢያቸው አቅመ ደካሞችን በማገዝ፣ ዘመድ አዝማድን በመጠየቅ፣ እንግዶችን በማስተናገድና መልካም ምኞትን በመለዋወጥ በማክበር ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። 1ሺህ 501ኛው የነብዩ ሙሐመድ የልደት በዓል በጂንካ ከተማ የተከበረው በተለያዩ ሃይማኖታዊ ሥርአቶችና ማዕድ ማጋራት መሆኑ ታውቋል።
የመውሊድ በዓልን ስናከብር የነብዩ ሙሀመድን አስተምህሮን በመተግበር መሆን አለበት
Aug 25, 2026 94
ጎንደር ፤ነሀሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የመውሊድ በዓልን ስናከብር የነብዩ ሙሀመድን አስተምህሮ በመተግበር መሆን እንዳለበት በጎንደር ከተማ የእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ስብሳቢ ሼህ ኢብራሒም ሙሐመድ ገለጹ። በጎንደር ከተማ የመውሊድ በዓል በጀሚ አልከቢር መስጂድ በድምቀት ተከብሯል። የምክር ቤቱ ዋና ሰብሳቢ ሸህ ኢብራሒም ሙሐመድ በበዓሉ ላይ እንደገለጹት የነቢዩ ሙሐመድ መወለድ በአስተምህሯቸው አማካኝነት ለሰው ልጆች ፍቅር፣ ሠላምና እኩልነት መስፈን ትልቅ አጋጣሚ ፈጥሯል። በአሉ ሲከበር ሀይማኖታዊ አስተምህሮውን በመተግበር ሊሆን እንደሚገባ አመልክተዋል ። በአሉን በመረዳዳትና በጋራ ማክበር እንደሚገባም አስገንዝበዋል ። ወጣቱም የበአሉን የፍቅርና የመከባበር እሴት በመረከብ ለቀጣይ ትውልድ ማስተላለፍ እንዳለበት አሳስበዋል። የበዓሉ ታዳሚ አቶ አስረስ ሙሐመድ በበኩላቸው የመውሊድ በዓል በህዝበ ሙስሊሙ ዘንድ በደስታ የሚጠበቅና የሚከበር ነው ብለዋል። በዓሉን ሃይማኖታዊ አስተምህሮው በሚያዘው መሰረት ምስኪኖችንና አቅም የሌላቸውን ወገኖች በመደገፍ እያከበርን ነው ብለዋል። በዓሉን በጸሎትና በሌሎች ሃይማኖታዊ ስርዓቶች እያከበሩ መሆኑን የገለጹት ደግሞ ሼህ ሙሀመድ አህመድ ናቸው። በአሉን በጋራ በመሆን በፍቅርና በመተሳሰብ እያከበሩ መሆናቸውን ጨምረው ገልጸዋል ። በጎንደር ከተማ የመውሊድ በአል የሀይማኖት አባቶችና ምአመናን በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል።
የመውሊድ በዓልን ፍቅርና አብሮነትን በሚያጎለብቱ ተግባራት እያከበርን ነው - በዲላ የእምነቱ ተከታዮች
Aug 25, 2026 87
ዲላ፣ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ) ፦ የመውሊድ በዓልን ፍቅርና አብሮነትን በሚያጎለብቱ ተግባራት እያከበሩ መሆናቸውን በዲላ ከተማ የእምነቱ ተከታዮች ገለጹ። በዲላ ከተማ 1ሺህ 501ኛ የመውሊድ በዓልን ምክንያት በማድረግ ከ2 ሺህ ለሚልቁ ወገኖች ማዕድ የማጋራት መርሀግብር ተከናውኗል። በከተማው የሰላም መስጅድ ኢማም ሼህ ሶፍያን ጀማል ለኢዜአ እንደገለጹት በዓሉ በህዝበ ሙስሊም ዘንድ ትልቅ ስፍራ የሚሰጠው ሲሆን በዓሉንም ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን ጠብቀው በፍቅርና በንድነት እያከበሩት ይገኛሉ። በዓሉ ያሉትን የአብሮነትና የመረዳዳት እሴቶች በሚያጎለበት መልኩ ለማክበርም ከ2ሺህ ለሚልቁ ወገኖች ማዕድ የማጋራት ሥራ መከናወኑን ተናግረዋል። የመውሊድን በዓል ስናከብር የነብዩ መሐመድን በጎ አርአያነት በመከተል የተቸገሩትን በመርዳትና በአብሮነት ሊሆን ይገባል ያሉት ደግሞ በከተማው የቢላል መስጅድ ኢማም ሼህ ሰይድ መሐመድ ናቸው። በዓሉን ሐይማኖታዊ ሥርዓቱን በጠበቀ መልኩ በሃይማኖታዊ ትምህርት፣ በመረዳዳት፣ በፍቅርና በአንድነት እያከበሩ መሆናቸውንም ገልጸዋል። ከእምነቱ ተከታዮች መካከል ኡስታዝ አሊ ነጋሽ በበኩላቸው የመውሊድን በዓል በሃይማኖታዊ አስተምህሮ በሚፈቅደው መሰረት በበጎ ሥራ እያከበሩት መሆናቸውን ተናግረዋል። በመውሊድ በዓል እርስ በርስ ያለንን አንድነት፣ ፍቅርና መደጋገፍ በማጠናከር የነብዩ መሀመድን አርአያነት በተግባር ማሳየት አለብን ሲሉም አክለዋል።
ለተማሪዎች የተደረገው ድጋፍ የተሻለ ውጤት አስገኝቷል
Aug 25, 2026 104
አዳማ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ተማሪዎች ሙሉ ጊዜያቸውን በትምህርታቸው ላይ ብቻ እንዲያውሉ በመደረጉ የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ መቻላቸውን የኦልማ የአዳማ ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤት እና የዶዶላ ኢፋ ቦሩ ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህራን ገለጹ። በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤቶች በሀገር አቀፍና በክልል ደረጃ የላቀ ውጤት የሚያስመዘግቡ ተማሪዎችን ለማፍራት ታስበው የተቋቋሙ ናቸው። በኦሮሚያ ልማት ማህበር (ኦልማ) የአዳማ ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር አቶ አበበ ዘውዴ ለኢዜአ እንደገለፁት በዘንድሮው የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ከፍተኛ ውጤት በትምህርት ቤቱ ተመዝግቧል። የመማር ማስተማር ዕቅዱን የጋራ በማድረግና መምህራን ከመደበኛ ማስተማር ባለፈ ለተማሪዎች እንደ በርካታ ድጋፎችን እንዲሰጡ በመደረጉ፣ ተማሪዎች ትኩረታቸውን በትምህርታቸው ላይ ብቻ እንዲያደርጉ ማስቻሉን ገልጸዋል። በተለይም በሀገር አቀፍ ፈተና ዝግጅት ወቅት ከተከታታይ የጥናት መርሃ-ግብር እስከ ሞዴልና ማጠቃለያ ፈተናዎች ድረስ በማዘጋጀት ለፈተናው ብቁ የሚያደርጋቸውን ልምድ እንዲቀስሙ መደረጉን ገልጸዋል። በተጨማሪም የመማር ማስተማር ሂደቱን ተማሪ ተኮር በማድረግ በንድፈ-ሀሳብ የተማሩትን በቤተ-ሙከራ በተግባር አረጋግጠው ሪፖርት እንዲያቀርቡ በመደረጉ ለፈተናው በበቂ ሁኔታ እንዲዘጋጁ መደረጉን ገልጸዋል። በዚህም በዘንድሮው የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ከፍተኛውን ውጤት በማስመዝገብ ቀዳሚ መሆን መቻላቸውን ገልጸዋል። የዶዶላ ኢፋ ቦሩ ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር አቶ ዴቱ ዲቦ በበኩላቸው፤ ለስኬት ዋናው ምስጢር ተማሪዎችን ለሀገር አቀፍ ፈተናው በተገቢው መንገድ ማዘጋጀት መቻላቸው መሆኑን ገልጸዋል። ተማሪዎች ጊዜያቸውን በአግባቡ በመጠቀም በቤተ-ሙከራዎች፣ በአይሲቲ ክፍሎችና በቤተ-መጻሕፍት በአግባቡ እንዲገለገሉና እንዲያጠኑ በመደረጉ የተገኘ ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት በትምህርት ቤቱ በሀገር ደረጃ ቀዳሚ ውጤት መመዝገቡን ያነሱት ርዕሰ መምህሩ፣ ሀገርና ትውልድን ለመገንባት የሚደረገውን ጥረት ለማሳካት በትምህርት ጥራት ላይ በትኩረት እየሰሩ ለመሆኑ ማሳያ ነው ብለዋል። በዚህም በትምህርት ቤቱ ለሁለተኛ ጊዜ በዘንድሮው የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና በተማሪ ሳዳም አብዱልአዚዝ በማህበራዊ ሳይንስ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገቡን አክለው ገልጸዋል። በኦልማ የአዳማ ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤት 591 ነጥብ 6 ያመጣው ተማሪ ጃለል ግርማ እንዳለው፣ ሙሉ ጊዜውን በትምህርትና በጥናት ላይ በማዋሉ ይህንን ከፍተኛ ውጤት ማምጣት ችሏል። የስኬቱ ሚስጥርም ጠንክሮ መስራትና ሙሉ ጊዜን ለጥናት መስጠት መሆኑን ተናግሯል። በዶዶላ ኢፋ ቦሩ ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤት ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገበው ተማሪ ሳዳም አብዱልአዚዝ በበኩሉ፤ በምዕራብ ሐረርጌ ጭሮ ከተማ የ8ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተና ከፍተኛ ውጤት በማምጣት ተወዳድሮ ወደ ዶዶላ ኢፋ ቦሩ ልዩ አዳሪ ትምህርት ቤት መግባቱን ገልጿል። "የስኬቴ ሚስጥር ጠንክሮ መስራትና ማጥናት ነው" ያለው ተማሪ ሳዳም፣ ይህንን ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ የቻለው ሙሉ ጊዜውን በጥናት ላይ በማሳለፉና በዕቅድ በመመራቱ መሆኑን ገልጸዋል። "ውጤት የሚገኘው በለፉበት ልክ ነው" ያለው ተማሪ ሳዳም፣ በርትቶ በማጠናቱ 576 ነጥብ 25 የሆነ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ተናግሯል።
ኢትዮጵያ በዲጂታል ጤና ሥርዓት በሽታን በመከላከልና አክሞ በማዳን ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበች ነው - ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ
Aug 25, 2026 159
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በዲጂታል ጤና ሥርዓት በሽታን በመከላከልና አክሞ በማዳን ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበች መሆኑን የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ገለጹ። 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባኤ በአዲስ አበባ ዓድዋ ድል መታሰቢያ መካሄድ ጀምሯል። በመርሃ ግብሩ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ፣ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ፣ሀገራት የጤና ሚኒስትሮች፣ የቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ የጤና ተቋማት መሪዎች ተገኝተዋል። 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባኤ የቀጣናውን የጤና አጀንዳ በመቅረፅ፣ ትብብርን በማጠናከር እና በአሕጉሪቱ ጤናማ፣ ደህንነቱ የተጠበቀና ፈተናዎችን የሚቋቋም ማህበረሰብ መገንባት ያስችላል። ከዚህ አንፃር ኢትዮጵያ መድረኩን ማዘጋጀቷ በቀጣናው በትብብር ላይ የተመሰረተ የጤና ስርዓት ለመፍጠር ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት ያሳያል። ኢትዮጵያ ከዓለም ጤና ድርጅትና ከሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበር የጤና ስርዓቷን በማጠናከር እና ሀገራዊ ትኩረት የሚሰጣቸው የጤና ጉዳዮችን በማሳካት በኩል ያስመዘገበችውን መሻሻል ለማሳየት ዕድል ይፈጥራል። በኢትዮጵያ መሰረታዊ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ማስፋት፣ የጤና ስርዓት አፈፃፀምን ማጠናከር እና የማርበርግ ቫይረስ በሽታ ወረርሽኝን በተሳካ ሁኔታ መቆጣጠርን ጨምሮ የተመዘገቡ ስኬቶች አይበገሬ የጤና ስርዓት ለመገንባት ያላትን ዘላቂ ጥረት የሚያሳይ ነው። የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች በጤና ስርዓቱ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እያሳደሩ ነው። ኢትዮጵያ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትንና ጥራትን በዘላቂነት ለማሻሻል ብሔራዊ የጤና ስትራቴጂ ቀርፃ እየሰራች መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የህክምና ባለሙያዎችን በማብቃትና የህክምና መገልገያዎችን በማዘመን የእናቶችና ህፃናትን ሞት በመሰረታዊነት መቀነስ ተችሏል ብለዋል። የዲጂታል የጤና ስርዓትን በማሳደግ የጤና እና የቴክኖሎጂ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል አቅም እየተፈጠረ መሆኑንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የዓለም ጤና ድርጅት የማቹሪቲ ሌቭል 3 መድረሷን ገልጸው፤ የሀገር ውስጥ ምርት ከኢንዱስትሪ ፖሊሲ ያለፈ የጤና ስትራቴጂ ነው ብለዋል። ቴክኖሎጂ በዜጎች የጤና ሥርዓት ላይ መሰረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑን በማንሳት፤ ከኮቪድ 19 ወረርሽኝ ብዙ ልምድ መገኘቱን ተናግረዋል። አፍሪካ የዕውቀትና የክህሎት ችግር የለባትም፣ ያለውን የተፈጥሮ ሀብት አሟጦ መጠቀም ይገባል ብለዋል። ለአፍሪካ የጤና ሉዓላዊነት የሀገር ውስጥ ምርት ወሳኝ መሆኑን በማንሳት፣ ኢትዮጵያ ከአፍሪካውያን ጋር በትብብር ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል።
የጤና ሥርዓትን በዲጂታል ቴክኖሎጂና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ማጠናከር ለአፍሪካ የወደፊት የጤና ሉዓላዊነት ቁልፍ ነው
Aug 25, 2026 69
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የጤና ሥርዓትን በዲጂታል ቴክኖሎጂና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ማጠናከር ለአፍሪካ የወደፊት የጤና ሉዓላዊነት ቁልፍ መሆኑን በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የሥራ አስፈፃሚ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቦባክሪ ዲያው ገለጹ። 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ጉባኤ በዓድዋ ድል መታሰቢያ እየተካሄደ ነው። በመርሀግብሩ የኢፌዴሪ ፕሬዝደንት ታዬ አጽቀስላሴ፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ፣ የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር መሀመድ ያኩብ ጃናቢ ተገኝተዋል። በተጨማሪም ከ47ቱ የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ አባል ሀገራት የተውጣጡ የጤና ሚኒስትሮች፣ ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች፣ የጤና ባለሙያዎች፣ የልማት አጋሮች እንዲሁም የቀጣናውና የዓለም አቀፍ ድርጅቶች መሪዎች ታድመዋል። ጉባኤው በጤና ዘርፍ በአምስት ምሰሶዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ይካሄዳል። እነኚህም በአፍሪካ ዘላቂ የጤና ፋይናንስ ስርዓት መገንባት፣ የመጀመሪያ ደረጃ የጤና ክብካቤ፣ ዲጂታል የጤና ስርዓት መገንባት፣ የጤና ባለሙያዎች አቅም ግንባታና የሀገር ውስጥ ምርቶችን ማሳደግ ናቸው። በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የሥራ አስፈፃሚ ጽሕፈት ቤት ሀላፊ አቦባክሪ ዲያው በዚሁ ወቅት እንዳሉት የውጭ የጤና ድጋፍ መቀነስ፣ ደካማ የፋይናንስ አቅም እና የትግበራ ክፍተት በቀጣናው የጤና ስርዓት ላይ ተጽዕኖ ማሳደሩን ጠቅሰዋል። የጤና ሉዓላዊነት ማለት አፍሪካ የራሷን የጤና ቅድሚያዎች በራሷ የመወሰን፣ የጤና ሥርዓቶቿን የመደጎም፣ መረጃዎቿን የማስተዳደር፣ አስፈላጊ የጤና ምርቶችን በራሷ የማምረት እና ወደፊት ሊያጋጥሙ ከሚችሉ ቀውሶች ሕዝቦቿን የመጠበቅ አቅም ማለት ነው ብለዋል። ጤናን ከመደበኛ ማኅበራዊ ወጪ ወደ ምርታማ ኢኮኖሚያዊ ኢንቨስትመንት መቀየር እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የተበታተነ አሠራርን ወደ አንድ ተአማኒ የአሰራር ሁኔታ ማምጣት እንደሚገባ ነው ያመላከቱት። ኢትዮጵያ በዲጂታል መለያ፣ የጤና መረጃ ሥርዓቶች ተናባቢነት፣ የወጪ አፈጻጸምን መከታተልና በመረጃ የተደገፈና በሰው ሠራሽ አስተውሎት የታገዘ ውሳኔ አሰጣጥ በአንድ ላይ ማጠናከር እንደሚቻል ማሳያ መሆኗን ጠቅሰዋል። የዓለም ጤና ድርጅት እና የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የሚያከናውኗቸው ሥራዎች እጅግ ተደጋጋፊ መሆናቸውንም ገልጸዋል። የጤና ሥርዓትን በዲጂታል ቴክኖሎጂና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ማጠናከር ለአፍሪካ የወደፊት የጤና ሉዓላዊነት ቁልፍ መሆኑን ተናግረዋል።
የመውሊድን በዓል አንድነትንና መደጋገፍን በሚያጠናክር መልኩ ማክበር ይገባል
Aug 25, 2026 84
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የመውሊድን በዓል አንድነትንና መረዳዳትን በሚያጠናክር መልኩ ማክበር እንደሚገባ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት አስገነዘበ። የዘንድሮው 1ሺህ 501ኛ የመውሊድ በዓል በታላቁ አንዋር መስጂድ በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስርዓቶች በመከበር ላይ ነው። የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንት ሼህ አብዱልከሪም በድረዲን በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት የመውሊድን በዓል የአንድነትንና መረዳዳትን በሚያጠናክር መልኩ ማክበር እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በዓሉን ድጋፍ ከሚያስፈልጋቸው ወገኖች ጋር አብሮ ማክበር እንደሚገባም ገልጸዋል። ሼህ አብዱልከሪም ዘለቂ ሰላምን፣ ልማትንና አንድነትን ለማስጠበቅ ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ሼህ መሐመድ ሸሪፍ በበኩላቸው፣ የመውሊድ በዓል የነብዩ መሀመድን አርአያነት በተግባር በማሳየት ማክበር ይገባል ብለዋል።
የመውሊድ በዓል በአብሮነት እና እርስ በርስ በመረዳዳት እያከበርን ነው - የእምነቱ ተከታዮች
Aug 25, 2026 93
ሐረር፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የመውሊድ በዓል በፍቅር፣ በአብሮነት እና እርስ በርስ በመረዳዳት እያከበሩ መሆኑን በሐረር የእምነቱ ተከታዮች ገለጹ። 1 ሺህ 501ኛው የመውሊድ በዓል በሐረር ከተማ የሃይማኖት አባቶች፣ የእምነቱ ተከታዮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ከማለዳው ጀምሮ በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስነ-ስርዓቶች በመከበር ላይ ይገኛል። የበዓሉ ታዳሚዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የመውሊድ በዓልን በፍቅር፣ በአብሮነት፣ እርስ በርስ በመጠያየቅና በመረዳዳት በደመቀ ሁኔታ እያከበሩት ይገኛሉ። ከበዓሉ ተሳታፊዎች መካከል አቶ ሳላህ ዩሱፍ፤ "የመውሊድ በዓል በሰዎች መካከል ፍቅርን፣ አብሮነትን፣ አንድነትንና የመረዳዳት ባህልን የሚያጠናክር ነው" ሲሉ ገልጸዋል። አክለውም በዓሉን ሃይማኖታዊ ስርዓቱ በሚያዘው መሰረት በድምቀት እያከበሩት እንደሚገኙ ገልጸዋል። ሌላው የበዓሉ ተሳታፊ ወጣት ዚያድ አርጋው በበኩሉ፤ የመውሊድ በዓልን ከሌሎች ወንድምና እህቶቹ ጋር አብሮነትን በማጠናከር በሰላምና በደስታ እያሳለፈ እንደሚገኝ ተናግሯል። አክለውም በዓሉን የነቢዩ መሀመድን አስተምህሮ በመከተል የተቸገሩትን በመርዳትና በመደገፍ እያከበረ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ወጣት ያስሚን ሙክታር በበኩሏ፤ የነቢዩ መሐመድ መውሊድን በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስነ-ስርዓቶች ከማክበር ባሻገር በጎ ሥራዎችን በማከናወንና ያላቸውን ለሌሎች በማካፈል ማከበር እንደሚገባ ተናግራለች። የመውሊድ በዓልን ሃይማኖታዊ አስተምህሮውን በጠበቀ መልኩ በድምቀት እያከበሩ እንደሚገኙ ሌላው የበዓሉ ተሳታፊ ኢማድ ሳለሃዲን ገልጸዋል። አክለውም በዓሉን ያላቸውን በማካፈል፣ በመረዳዳትና አንድነትን በማጠናከር የነብዩ መሐመድን መልካም ተግባራት በማስታወስ እያከበሩት እንደሚገኙ ገልጸዋል።
አፍሪካውያን በዓለም የጤና ስርዓት ሪፎርም ላይ በንቃት በመሳተፍ የጋራ አቋም መያዝ አለባቸው - የዓለም ጤና ድርጅት
Aug 25, 2026 187
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ አፍሪካውያን በዓለም የጤና ስርዓት ሪፎርም ላይ በንቃት በመሳተፍ የጋራ አቋም መያዝ እንዳለባቸው የዓለም ጤና ድርጅት ገለጸ። 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ስብሰባ በአዲስ አበባ ዓድዋ ድል መታሰቢያ መካሄድ ጀምሯል። በመርሃ ግብሩ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ፣ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ፣ የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር መሀመድ ያኩብ ጃናቢ፣ የአፍሪካ ሀገራት የጤና ሚኒስትሮች፣ የቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ የጤና ተቋማት መሪዎች ተገኝተዋል። የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም ስብሰባውን በተመለከተ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት እንዳሉት፤ አፍሪካ የሚከሰቱ ወረርሽኞችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚወስዱት እርምጃ ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው። የአፍሪካ በሽታን የመከላከልና የመቆጣጠር አቅም እያደገ መምጣቱን ገልጸው፤ ሀገራት ትብብራቸውን ማጠናከር አለባቸው ብለዋል። ኢትዮጵያ የማርበርግ ወረርሽኝን በ90 ቀናት ብቻ መቆጣጠርና ማጥፋት መቻሏ የአፍሪካውያን የማድረግ አቅም እያደገ ለመምጣቱ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። በአፍሪካ ዕምቅ ዕውቀትና የተፈጥሮ ሀብት እንዳለ በማንሳት፣ የሀገር ውስጥ የመድሀኒትና የህክምና መገልገያ ግብዓቶችን ምርት ማሳደግ ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያን ጨምሮ ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት የዓለም ጤና ድርጅት የማቹሪቲ ሌቭል 3 መድረሳቸውንም ዋና ዳይሬክተሩ ጨምረው አስታውቀዋል። አፍሪካውያን ትብብራቸውን በማጠናከር ከውጭ ጣልቃ ገብነት ነፃ ሆነው የሀገር ውስጥ ምርታቸውን ማሳደግ እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። በቀጣይም የአፍሪካን የጤና ስርዓት በአፍሪካ አቅም ለመገንባት ቀጣይነት ያለው የፋይናንስ ምንጭ መፍጠር አለባቸው ብለዋል። በዓለም የጤና ስርዓት ሪፎርም ላይ ንቁ ተሳታፊ መሆን የሚያስችላቸውን ትብብርና ቅንጅት መፍጠር ይገባቸዋል ሲሉም ገልጸዋል። የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር መሐመድ ያኩብ ጃናቢ በበኩላቸው፣ ጉባኤው የአፍሪካ የጤና ችግሮች ላይ የጋራ ውይይት በማድረግ የጋራ የመፍትሔ ሀሳብ የሚፈልቅበት መድረክ መሆኑን ገልጸዋል። በአፍሪካ በመሪዎች ቁርጠኝነት የአህጉሪቱን ግዙፍ የህዝብ ቁጥር የሚመጥን የጤና ተቋማትና የባለሙያ ዝግጁነት በመገንባት በጤና ሥርዓቱ የመጣውን መሻሻል ማስቀጠል እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል። በአፍሪካ ለተመዘገበው የጤና አገልግሎት መሻሻል የዓለም ጤና ድርጅት ያልተቋረጠ ድጋፍ ማድረጉን በመግለጽ፣ የአፍሪካን የጤና ኢንቨስትመንት በማሳደግ የራስ አቅም ማጎልበትም አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰዋል። የጤና ሥርዓት ዝማኔ አመራር፣ ኢንቨስትመንትና ትብብር እንደሚጠይቅ ጠቁመው፣ የዓለም ጤና ድርጅት አፍሪካ አቅሟን እንድትገነባ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
በዓሉን በጋራ እና አቅመ ደካሞችን በመደገፍ እያከበርን ነው - የሃይማኖት አባቶችና ምዕመናን
Aug 25, 2026 88
ጅማ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የመውሊድ በዓልን በጋራ እና አቅመ ደካሞችን በመደገፍ እያከበርን ነው ሲሉ የጅማ ከተማ የሃይማኖት አባቶችና የእምነቱ ተከታዮች ገለጹ። 1 ሺህ 501ኛው የመውሊድ በዓል በጅማ ከተማና አካባቢው በደማቅ ሁኔታ እየተከበረ ይገኛል። በዓሉ በተለይም በጅማ መድረሰቱል ከይርያ ቅጥር ግቢ ውስጥ በመተሳሰብ፣ በመረዳዳትና አቅመ ደካሞችን በመመገብ እየተከበረ ነው። የጅማ ታላቁ ሙኒር መስጂድ ኢማም ሼህ መሐመድ አባዲጋ፣ መውሊድን ስናከብር የተቸገሩ ወገኖችን በማሰብና በመረዳዳት በጋራ ሊሆን ይገባል ብለዋል። መውሊድ የደስታና የሰላም በዓል መሆኑን የጠቀሱት ሼህ መሐመድ፤ የተቸገረን በመጠየቅ፣ የተራበን በመመገብ፣ የተራቆተን በማልበስ እና ለሌሎች ደስታ በመሆን ልናስበው ይገባል ብለዋል። ይህንን በዓል ምክንያት በማድረግም ከአምስት ሺህ በላይ አቅመ ደካሞችን መመገብ መቻሉን ተናግረዋል። ሌላው የእምነቱ ተከታይ አባስ አብዱሰላም በበኩሉ፣ የመውሊድ በዓል ትርጉሙ የሚሟላው የተቸገሩትን ስናስብና ለሌሎች ደስታ ስንሆን ነው ብሏል። ከትናንት ጀምሮ ከጎሮቤትና በአካባቢው የሚገኙ አቅመ ደካሞችን በመርዳት እያሳለፈ መሆኑን የገለጸው አባስ፣ ይህንን በጎ ተግባር ወደፊትም እንደሚቀጥል ተናግሯል። በበዓል ወቅት ብቻ ሳይሆን በማንኛውም ጊዜ መደጋገፍና በጋራ መኖር እንደሚያስፈልግ የገለጹት ደግሞ አሚር ጠሃ እና በሀቁ ኑሩ ናቸው። በተለይም በመውሊድ በዓል ወቅት ይህንን የመረዳዳትና የመተሳሰብ ባህል ማጠናከር እንደሚገባም ጠቁመዋል። በጅማ ከተማ የሚከበረው የመውሊድ በዓል ሃይማኖታዊ እሴቱን በመጠበቅ በመተሳሰብና በመረዳዳት በጋራ እየተከበረ መሆኑ ተገልጿል።