ማህበራዊ
በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል--ትምህርት ቢሮ
Oct 21, 2024 81
ሐዋሳ፤ ጥቅምት 11/2017(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና ትምህርት ቢሮ ሃላፊ አቶ በየነ በራሳ ገለጹ። በክልሉ ብላቴ ዙሪያ ወረዳ በ"በሌላ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት" በኢትዮጵያ የጃፓን ኤምባሲ የገንዘብ ድጋፍ የተገነባ ማስፋፊያ ፕሮጀክት ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።   አቶ በየነ በራሳ በዚህ ጊዜ እንደተናገሩት በክልሉ ያጋጠመውን የትምህርት ስብራት ለመጠገን ክልል አቀፍ የትምህርት ተሃድሶ ፕሮግራም ተቀርጾ ወደ ሥራ ተገብቷል። ፕሮግራሙ ከቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ጀምሮ ትኩረት ተደርጎ የሚሰራበት በመሆኑ ችግሩን ከስሩ ለማስተካከል አቅም እየፈጠረና የትምህርት ቤቶችን ገጽታ የቀየረ መሆኑንም አስረድተዋል።   በዚህም ተስፋ ሰጪ ውጤቶች መታየታቸውን ጠቁመው፣ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የተጀመረው ሥራ ለትምህርት ጥራት ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና ስላለው ቅንጅታዊ ስራው ይጠናከራል ብለዋል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ አክለውም "የጃፓን ኤምባሲ ለትምህርቱ ዘርፍ እያደረገ ያለው ድጋፍ በክልሉ የትምህርት ጥራት ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን የሚያግዝ ነው" ብለዋል። በኤምባሲው ድጋፍ የተገነባው የማስፋፊያ ፕሮጀክት በአጭር ጊዜ ውስጥ መጠናቀቁን ጠቅሰው፣ ለፕሮጀክቱ ውጤታማነት አስተዋጾ ላደረጉ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል። በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ሺባታ ሂሮኖሪ በበኩላቸው ኢትዮጵያና ጃፓን በርካታ አመታትን ያስቆጠረ ወዳጅነት እንዳላቸው ጠቅሰው ትምህርትን ጨምሮ የማህበረሰቡን ህይወት በሚቀይሩ የልማት ፕሮጀክቶች በትብብር እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   የትምህርት ስራን መደገፍ ትውልድ ላይ መስራት በመሆኑ የጃፓን መንግስት ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም የገለጹት አምባሳደሩ በሲዳማ ክልል ባለፉት አምስት ዓመታት ከ6 በላይ ትምህርት ቤቶች ግንባታ መከናወኑን ተናግረዋል። በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ለተጀመረው ስራ ስኬታማነት የጃፓን የትምህርት ባለሙያዎች ድጋፍ እያደረጉ ሲሆን በግብርናው ዘርፍም የጃፓን መንግስት ከክልሉ ጋር እየሰራ ነው ብለዋል። የበሌላ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ማስፋፊያ ፕሮጀክት በተለያዩ አካላት ድጋፍ ከ8 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መገንባቱን የገለጹት ደግሞ ፕሮጀክቱን በበላይነት ሲከታተል የነበረው "ሪሰረክሽን ኤንድ ላይፍ ዴቬሎፕመንት" የተሰኘ ድርጅት አስፈጻሚ ዳይሬክተር አቶ ቢንያም በላቸው ናቸው። በፕሮጀቱ አራት የመማሪያ ክፍሎች፣ የመጸዳጃ ቤቶችና የመማሪያ ግብዓት መሟላታቸውን ገልጸው፣ ፕሮጀክቱ ቀጣይ ምዕራፎች እንዳሉትም ጠቁመዋል። የትምህርት ቤቱ ርዕሰ መምህር ፍቅሩ እስራኤል በትምህርት ቤቱ ከ3ሺህ 200 በላይ ተማሪዎች ትምህርታቸውን እንደሚከታተሉ ገልጸው፣ በትምህርት ቤቱ የመማሪያ ክፍል ጥበት እንደነበር አስታውሰዋል:: የፕሮጀክቱ ግንባታ በትምህርት ቤቱ የክፍል-ተማሪ ጥምርታን በማስተካከል በኩል ጠቀሜታ እንዳለውም አስረድተዋል። በፕሮጀክቱ ማስመረቂያ መርሃ ግብር ላይ ከጃፓን ኤምባሲ፣ ከሲዳማ ክልል የሚመለከታቸው አካላትና የህብረተሰብ ተወካዮች ተገኝተዋል።  
ዘራፊውን እና ፅንፈኛውን ቡድን በማፅዳት የአማራ ክልልን ወደ ቀደመ ሰላሙ እንዲመለስ እየተሠራ ነው
Oct 21, 2024 114
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 11/2017(ኢዜአ)፦ ዘራፊውን እና ፅንፈኛውን ቡድን በማፅዳት ክልሉ ወደ ቀደመ ሰላሙ እንዲመለስ የምስራቅ ዕዝ ኮር ሠራዊት ተልዕኮውን ውጤታማ በሆነ መንገድ መፈፀሙን የኮሩ አዛዥ ብርጋዲየር ጄኔራል አዲሱ መሃመድ ገለጹ። የኮሩ አዛዥ ብርጋዲየር ጄኔራል አዲሱ መሃመድ ሰራዊቱ በቁንዝላ፣ በአዴት፣ በብራቃት፣ በመሸንቲ፣ በቅንባባ፣ በወንጅ ኮለላ፣ በጭስ አባይ እና ሌሎች አካባቢዎች ላይ ባደረገው ስምሪት ከፍተኛ የፅንፈኛውን አመራሮች ከጥቅም ውጭ ሲያደርግ የተለያዩ የጦር መሳሪያዎችን ማርኳል ብለዋል።   በእነዚህ ስምሪቶች ብርሃኑ ፀጋዬ፣ ዘውዱ ላቀው፣ ፀጋ ፀዳለና ዘላለም አለሙ የተባሉ የፅንፈኛው አመራሮችን መደምሰስ መቻሉንም ተናግረዋል። ፅንፈኛው ቡድን ከሕዝብ የዘረፈውና ይገለገልበት የነበረውን አንድ አምቡላንስ፣ ሶስት ሃይሉክስ መኪና፣ አንድ ሲንግል ጋቢና ፓትሮል፣ 2 ባጃጅ፣ 36 ሞተር ሳይክል እንዲሁም በርካታ ኋላቀር መሳሪያ፣ ክላሽና ብትን ጥይቶችን በቁጥጥር ስር መዋሉን ብርጋዲየር ጄኔራል አዲሱ መሃመድ ገልጸዋል።   ህዝቡ በፅንፈኛው ሃይል ፕሮፖጋንዳ ሳይታለል ከፀጥታ ኃይሉ ጎን በመሆን አካባቢውን እንዲጠብቅም መልዕክት ማስተላለፋቸውን ከአገር መከላከያ ሰራዊት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የማይጨው ለምለም ካርል ሆስፒታል ለ220  የዓይን ሞራ ግርዶሽ ህሙማን ህክምና ሰጠ
Oct 21, 2024 83
መቀሌ፤ ጥቅምት 11/2017(ኢዜአ)፦ የማይጨው ለምለም ካርል አጠቃላይ ሆስፒታል ለ220 ሕሙማን የዓይን ሞራ ግርዶሽ ቀዶ ህክምና አደረገ። በማይጨው አጠቃላይ ለምለም ካርል ሆስፒታል የዓይን ቀዶ ህክምና ባለሙያ አቶ የማነ ግተት ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ሆስፒታሉ ከኦርቢስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ከመስከረም 07 እስከ ጥቅምት 10/2017 ዓ.ም ባሉ ቀናት በዓይን ሞራ ግርዶሽ በሽታ ለተጋለጡ 220 ህሙማን ነፃ የቀዶ ህክምና አገልግሎት ሰጥቷል። የዓይን ግርዶሽ በሽታ በዕድሜ መግፋትና የህክምና ክትትል ካለማድረግ እንደሚከሰት የተናገሩት አቶ የማነ፤ ህክምና ከተሰጣቸው የህሙማን ውስጥ 60 በመቶ የሚሆኑት እናቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። የዓይን ቀዶ ህክምናውን ለማካሄድ ኦርቢት ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ከሁለት ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያላቸው የህክምናና ለሌሎች አገልግሎቶች የሚውሉ ቁሳቁሶች እንዲሁም ልዩ ልዩ መድኃኒቶች ድጋፍ ማድረጉን ገልፀዋል። የህክምና አገልግሎት ከተደረገላቸው መካከል የ85 ዓመት ዕድሜ ባለፀጋ የእንዳመኾኒ ወረዳ ነዋሪ አቶ ተካ ግርማይ፤ ከሶስት ዓመታት በኋላ የዓይን ብርሃናቸው መመለሱን ገልፀዋል። የዓዲሽሁ ከተማ ነዋሪዋ ወይዘሮ ኪሮስ ተክለንቼአል በበኩላቸው፤ ሁለቱም ዓይኖቻቸው ማየት ተስኗቸው መቆየታቸውን ጠቅሰው፤ አሁን በተደረገላቸው ህክምና ለማየት መብቃታቸውን ተናግረዋል።    
ድርጅቱ ለአፋር ክልል ጤና ቢሮ የሞተር ብስክሌት ድጋፍ አደረገ
Oct 21, 2024 93
ሠመራ ፤ ጥቅምት 11/2017(ኢዜአ)፦ የዓለም ምግብ ድርጅት ለአፋር ክልል ጤና ቢሮ የሞተር ብስክሌት ድጋፍ አደረገ። አሥር የሞተር ብስክሌቶችን ለክልሉ ጤና ቢሮ ያስረከቡት በዓለም ምግብ ድርጅት የአፋር ክልል ተወካይ ፍሎረንስ ላንየሮ በወቅቱ እንዳሉት፤ ሞተር ብስክሌቶቹ በተለይም የጤና አገልግሎትን በአስቸጋሪ አካባቢዎች ተደራሽ ለማድረግ የሚረዱ ናቸው። ለማህበረሰብ ጤና ትኩረት በመስጠት አጋርነታችንን እንቀጥላለን ያሉት ተወካይዋ በዘርፉ ያሉትን ተግዳሮቶች ለመቀነስ ድርጅታቸው ጥረት እንደሚያደርግ ገልፀዋል። የአፋር ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ ያሲን ሐቢብ ዛሬ የተደረገው ድጋፍ በጤናው ዘርፍ ለሚከናወኑ የጤና አገልግሎት ስራዎች አጋዥ ናቸው ብለዋል። በተለይም በወረዳዎቹ የህፃናትና እናቶችን ጤንነት ከማስጠበቅ አንፃር ያላቸው ጠቀሜታ የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።   በክልሉ ለአስር ወረዳዎች የተደረገው የሞተር ብስክሌት ድጋፍ በገንዘብ ሲሰላ ከ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ መሆኑን ኃላፊው አስታውቀዋል። በስራ ቅልጥፍና እና ተደራሽነት ላይ አዎንታዊ ሚና የሚያበረክተው ይህን ድጋፍ ያደረገውን የዓለም ምግብ ድርጅትንም አመስግነዋል። ዛሬ የተደረገውን የሞተር ብስክሌት ድጋፍ ከተረከቡት መካከል የአብአላ ወረዳ ጤና ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኢብራሂም አሊሳ በበኩላቸው፤ ድጋፉ ለእናቶችና ህፃናት ጤና አገልግሎት ተደራሽነት አስፈላጊ ስራ የሚከናወንበት ነው ብለዋል። አብዛኛው የህብረተሰባችን ክፍል በገጠርና ራቅ ባለ አካባቢ ነዋሪ በመሆኑ በአካባቢው የሚገኙ የዘርፉ ባለሙያዎች እዚያ ደርሰው አገልግሎት እንዲሰጡ የሚያስችላቸው ነው ብለዋል። ድጋፍ የተደረገላቸው ወረዳዎች ኮነባ፣ ወሰማ፣ አብአላ፣ ጉሊና፣ አውራ፣ ኮሪ፣ ገረኒ፣ አደአርደዌ እና ሃንሩካ መሆናቸውም ተመላክቷል።  
በክልሉ ከጃፓን ኤምባሲ በተገኘ ከ8 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ የተገነባው የትምህርት ቤት ማስፋፊያ ፕሮጀክት ተመረቀ
Oct 21, 2024 136
ሀዋሳ ፤ጥቅምት 11/2017 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል ከጃፓን ኤምባሲ በተገኘ ከ8 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ በብላቴ ዙሪያ ወረዳ የተገነባው የበለላ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የማስፋፊያ ፕሮጀክት ግንባታ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉ ተገለፀ። የማስፋፊያ ፕሮጀክቱን ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ያደረጉት የሲዳማ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ኃላፈ አቶ በየነ በራሳና በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ሺባታ ሂሮኖሪ ናቸው። የማስፋፊያ ፕሮጀክት ግንባታውን ያከናወነው 'ሪዘሬክሽን ኤንድ ላይፍ ዴቬሎፕመንት ኦርጋናይዜሽን' የተሰኘው ድርጅት ዳይሬክተር አቶ ቢኒያም በላቸው ለኢዜአ እንዳሉት፤ የማስፋፊያ ፕሮጀክት ግንባታው የተጠናቀቀው በሁለት ወራት ጊዜ ውስጥ ነው። የማስፋፊያ ግንባታው አራት የመማሪያ ክፍሎችን፣ ሁለት ዘመናዊ መጸዳጃ ቤቶችን እንዲሁም ለቤተ ሙከራና ለመማር ማስተማር ተግባር የሚያገለግሉ ቁሳቁሶችን ያካተተ መሆኑንም ተናግረዋል ። የማስፋፊያ ፕሮጀክቱ ከ8 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበት ገልጸው ይህም ከጃፓን ኤምባሲ በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ የተከናወነ መሆኑም ተገልጿል። በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ የሲዳማ ክልል ከፍተኛ አመራሮችና የአካባቢው ማህበረሰብ ተወካዮች ተገኝተዋል።
በክልሉ አረጋዊያንን መደገፍና መንከባበብ የሁሉም ህብረተሰብ ክፍል ኃላፊነት ሊሆን ይገባል -ዶክተር ሙሉነሽ ደሴ
Oct 20, 2024 125
ባህር ዳር ፤ጥቅምት 10/2017 (ኢዜአ) ፡-በአማራ ክልል የሀገር ባለውለታ የሆኑ አረጋዊያንን መደገፍ፣ማገዝና መንከባከብ የሁሉም ህብረተሰብ ኃላፊነት ሊሆን እንደሚገባ በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ሙሉነሽ ደሴ ገለፁ። "ክብርና ፍቅር ለአረጋዊያን" በሚል መሪ ሃሳብ ዓለም አቀፍ የአረጋዊያን ቀን በባህር ዳር ከተማ ዛሬ ተከብሯል።   የቢሮ ኃላፊዋ በመድረኩ እንደገለፁት፤አረጋዊያን ለሀገር ትልቅ ዋጋ የከፈሉ ባለውለታዎች በመሆናቸው ያካበቱትን ዕውቀትና ክህሎት ለተተኪው ትውልድ እንዲያስረክቡ ምቹ ሁኔታ መፈጠር እንዳለበት ተናግረዋል። የአረጋውያን ገቢ ማስገኛ ማዕከላትን በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች በማስፋፋት ጧሪና ደጋፊ ለሌላቸው አረጋዊያን ለሚደረገው ድጋፍ የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን እገዛ ያደርጋል ብለዋል። በመሆኑም ሁሉም ህብረተሰብ ክፍል የሀገር ባለውለታ የሆኑ አረጋዊያንን በመደገፍና በመንከባከብ ሃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል። የክልሉ ሴቶች፣ህፃናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ብርቱካን ሲሳይ በበኩላቸው፤አረጋዊያን ለሀገራቸው ዕድገትና ለህዝባቸው አስተዋፅኦ ያበረከቱ ናቸው። አረጋዊያን በእርጅና ዘመናቸው ለከፋ ችግር እንዳይጋለጡ መንግስት፣ መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማትና ህብረተሰቡ በተቀናጀ አግባብ መደገፍና መንከባከብ እንደሚገባ ገልፀዋል።   በክልሉ መንግስት ቀደም ሲል በተገነባው የአረጋዊያን የገቢ ማስገኛ ህንፃ በሚገኝ ገቢ የከፋ ችግር ላለባቸው አንድ ሺህ 750 ለሚሆኑ አረጋዊያን በየወሩ በቋሚነት ቀጥታ ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል። እንዲሁም በሴፍቲኔት ፕሮግራምና ከህብረተሰቡ ገንዘብ በማሰባሰብ ጧሪና ደጋፊ ለሌላቸው ከ170 ሺህ በላይ አረጋዊያን ባለፈው ዓመት የቀጥታ ድጋፍ ተደርጓል ብለዋል። የአማራ ክልል አረጋዊያን ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ አምሳሉ መአዛው በበኩላቸው፤በባህር ዳር በተገነባው የአረጋዊያን የገቢ ማስገኛ ህንፃ በሚገኝ ገቢ ለከፋ ችግር የተጋለጡ አረጋዊያን በቋሚነት እየተደገፉ ነው። ይህን አጠናክሮ ለማስቀጠልም በየዞኑ እየተገነቡ የሚገኙ ተጨማሪ የገቢ ማስገኛ ህንፃዎች ሲጠናቀቁ ድጋፍ የሚደረግላቸው አረጋዊያን ቁጥር እያደገና ችግራቸው እየተቃለለ እንደሚመጣም ገልፀዋል። ህብረተሰቡም አረጋዊያንን በመደገፍና በመንከባከብ ለዘመናት ያካበቱትን ዕውቀትና ክህሎት ለመጭው ትውልድ እንዲያበረክቱ ማድረግ ይገባል ብለዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ34ኛ ጊዜ፣ በኢትዮጵያ ደግሞ ለ33ኛ ጊዜ በተከበረው የአረጋውያን ቀን ላይ የክልሉ የስራ ኃላፊዎች፣ አረጋዊያን የተገኙ ሲሆን በዕለቱም የማዕድ ማጋራትና አልባሳት ድጋፍ ተደርጓል።            
የበጎ ፍቃድ አገልግሎት እንቅስቃሴ የእድገት እና የአዎንታዊ ለውጥ መገለጫ ነው-ወይዘሮ ሙና አህመድ
Oct 20, 2024 116
ጅማ፣ጥቅምት 10/2017(ኢዜአ)፦የበጎ ፍቃድ አገልግሎት እንቅስቃሴ የእድገት እና የአዎንታዊ ለውጥ መገለጫ ነው ሲሉ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ሙና አህመድ ገለጹ። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የ2016 ዓ.ም የወጣቶች የበጎ ፍቃድ አገልግሎት የእውቅናና የማበረታቻ መርሃ ግብር በጅማ ከተማ ተካሄዷል። በመርሃ ግብሩ የሁሉም ክልሎች ተወካዮች፣የፌዴራል፣ የክልልና የዞን የስራ ሃላፊዎች እና በበጎ ፍቃድ አገልግሎት የተሳተፉ ወጣቶች ታድመዋል።   ሚኒስትር ዴኤታ ሙና በመርሃ ግብሩ እንደገለጹት ፥ የበጎ ፍቃድ እንቅስቃሴ የእድገት እና የአዎንታዊ ለውጥ መገለጫ ከመሆኑም ባለፈ የመተባበርና የአንድነት መሰረት ነው። ''በክረምት ወራት በተከናወኑ የበጎ ፍቃድ ተግባራት የአቅመ ደካማ ወገኖች ቤት ታድሷል፣ ደም በመለገስ የሰዎችን ህይወት መታደግ ተችሏል፣ ችግኝ በመትከል እና አካባቢን በማጽዳት በአካባቢ እንክብካቤ አበረታች ሥራ ተሰርቷል'' ብለዋል። የበጎ ፍቃድ ማህበራዊ አገልግሎቶች ሰብአዊነት የሚያጎለብት እና የመደጋገፍ ባህላችንን የምናስቀጥልበት መርሃግብር ነው ብለዋል። በተለይም ወጣትነት ለልማትና ለመልካም ተግባር እንዲሁም ለእድገትና ለእውቀት የተመቸ የእድሜ ክልል በመሆኑ፤ ወጣቶች በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ በመሳተፍ ይህንን ጊዜ ለበጎ ዓላማ መጠቀም ያስፈልጋል ሲሉም ገልጸዋል። የኦሮሚያ ክልል ወጣቶች እና ስፖርት ቢሮ ሃላፊ አቶ ማቴዎስ ሰቦቃ በበኩላቸው የክልሉ ወጣቶች የበጎነት መርህን ይዘው ወገኖቻቸውን በተለያየ የበጎ ስራዎች አገልግለዋል ብለዋል። በተለይም በክልሉ የበጎ ፍቃድ ማህበራዊ አገልግሎት የወገኖቻችንን ችግር በመለየት ለማገዝ እና ለመርዳት ጥረት የተደረገበት እንደነበር ገልጸው፤ ለወደፊትም የሚቀጥል እንደሆነ ገልጸዋል። ሚኒስቴሩ ጅማን ለዚህ መርሃግብር መምረጡን አመስግነው የከተማዋ ወጣቶችና ህብረተሰቡ በበጎ ፍቃድ ተግባራት ሲሳተፉ ቆይተዋል ያሉት ደግሞ የጅማ ከተማ ከንቲባ አቶ ጣሃ ቀመር ናቸው። ጅማ ብሔሮችና ብሔረሰቦች ተዋደውና ተዋልደው በፍቅር የሚኖሩባት ታሪካዊ ከተማ መሆኗን ገልጸው፤ ከተማዋን ውብ እና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚያስችሉ ልማቶች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። ከሲዳማ ክልል የመርሃግብሩ ተሳታፊ የሆነው ወጣት በረከት ሻለቃ በሰጠው አስተያየት ''በወጣትነት ጉልበታችን ወገኖቻችንን ማገዝ መቻላችን ትልቅ እድል ነው'' ብሏል ። ሌላው የጅማ ከተማ ወጣት ኑረዲን ሰማን፣ የመረዳዳት እና የመደጋገፍ ባህላችን በመሆኑ ህብረተሰባችንን ማገዝ እና አካባቢያችንን መጠበቅ እንቀጥልበታለን ነው ያለው።    
ኮርፖሬሽኑ በኢንዱስትሪ ፓርኮች አካባቢ ነዋሪዎችን በመሰረተ ልማት ተጠቃሚ ለማድረግ እየሰራ ነው
Oct 20, 2024 136
አዳማ፤ ጥቅምት 10/2017(ኢዜአ)፡- ከዋናው ተልዕኮ ጎን ለጎን በኢንዱስትሪ ፓርኮች አካባቢ ያሉ ነዋሪዎችን የመሰረተ ልማት ተጠቃሚ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ገለፀ። በኮርፖሬሽኑ ከ29 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ በአዳማ ከተማ ቶርበን ኦቦ ወረዳ የተገነባው የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሰሃ ይታገሱ (ዶ/ር) በትምህርት ቤቱ ምረቃት ወቅት እንደገለፁት ኢንዱስትሪ ፓርኩ ከዋናው ተልዕኮው ጎን ለጎን ማህበራዊ ሃላፊነቱን እየተወጣ ይገኛል።   በተለይም በኢንዱስትሪ ፓርኮቹ አካባቢ ያለውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ የትምህርት፣ የጤና፣ የመጠጥ ውሃና መንገድ የመሳሰሉ መሠረተ ልማቶችን ይገነባል ብለዋል። ለዚህም በአዳማ ከተማ ቶርበን ኦቦ ወረዳ የተገነባው የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት እንዱ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ትውልዱን በእውቀት ለመገንባት ለሚደረገው አገራዊ እንቅስቃሴ እገዛ አለው ብለዋል። ለቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቱ 29 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር ወጪ መደረጉን ገልጸው፤ በቀጣይም ትምህርት ቤቱን ወደ አንደኛ እና 2ኛ ደረጃ ለማሳደግ ቃል ገብተዋል።   የአዳማ ኢንዱስትሪ ፓርክ ስራ አስኪያጅ አቶ ጉልላት አበበ በበኩላቸው በፓርኩ 700 ሚሊዮን ዶላር ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች በስራ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። ፓርኩ 60 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አስገኝቷል ያሉት አቶ ጉልላት፤ ባለፈው በጀት ዓመት ከሶስት ቢሊዮን ብር በላይ ተኪ ምርት በማምረት ለሀገር ውስጥ ገበያ ማቅረቡንም ጨምረው ገልጸዋል። ፓርኩ ስምንት ሺህ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ ከትምህርት ቤቶች እድሳት፣ ጥገናና ግንባታ እንዲሁም የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በትምህርት ቤቱ ምረቃና ሥራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ ምክትል ሃላፊ ካሣሁን ገላና(ዶ/ር) በበኩላቸው በክልሉ ከሁለት ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ዕድሜያቸው ለትምህርት የደረሱ ልጆች የቅድመ መደበኛ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ ነው ብለዋል። በተለይም በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ እየተደረገ ያለው ጥረት የሚደገፍ መሆኑን አመልክተው ለዚህም የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በአዳማ ከተማ ቶርበን ኦቦ ወረዳ የገነባው የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት እንዱ ማሳያ ነው ብለዋል። ትምህርት ቤቱ 280 የቅድመ መደበኛ ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር መጀመሩንም ተናግረዋል። በከተማዋ አስተማማኝ ሰላምን ከማረጋገጥ ባለፈ ተተኪ ትውልድ ትምህርት እንዲያገኝ ለቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶች ግንባታ ትኩረት መሰጠቱን የገለጹት ደግሞ የአዳማ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ ሙላቱ ዲባ ናቸው።
የኢሬቻ በዓል በህዝቦች መካከል አብሮነትን ይበልጥ እያጠናከረ ነው -አባገዳዎችና የሀገር ሽማግሌዎች
Oct 20, 2024 93
ጋምቤላ፤ ጥቅምት 10/2017 (ኢዜአ)፦ የኢሬቻ በዓል በህዝቦች መካከል ያለውን አንድነትና አብሮነት ይበልጥ እያጠናከረ መሆኑን አባገዳዎችና የሀገር ሽማግሌዎች ገለፁ። በጋምቤላ የመልካ ባሮ ኢሬቻ በዓል ዛሬ እየተከበረ ነው።   ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል የሀገር ሽማግሌና አባገዳዎች ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ የኢሬቻ በዓል በአጎራባች ክልሎች መከበሩ የህዝቦችን አንድነትና አብሮነት ይበልጥ ለማጠናከር ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ብለዋል። የጋምቤላ ክልል የሀገር ሽማግሌ አቶ ፒተር አማን፣ የኦሮሚያ እና የጋምቤላ ክልሎች ህዝቦች የቆየ አንድነትና አብሮነት እንዳላቸው አመልክተዋል።   በመሆኑም የምስጋና፣ የሰላምና የይቅርታ መገለጫ የሆነው የኢሬቻ በዓል በጋምቤላ ክልል በዚህ መልኩ መከበሩ የህዝቡን አብሮነትና አንድነት ይበልጥ የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል። በበዓሉ ላይ የታደሙት አባ ገዳ ጎበና ሆላ በበኩላቸው የጋምቤላና የኦሮሚያ ክልል ህዝቦች ዘመናትን ያስቆጠረ የጋራ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስተጋብር ያላቸው ናቸው ብለዋል። የመልካ ባሮ ኢሬቻ በዓልን በጋራ ማክበራቸውም ለዘመናት የነበረውን ትስስርና አንድነት አፅንቶ ለትውልዱ ለማስተላለፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል። የኢሬቻ በዓል በአንድነትና በአብሮነት የሚከበር የሰላምና የፍቅር በዓል ነው ያሉት አባገዳ ጎበና፤ በዓሉን ስናከብር አንድነትንና መተሳሰብን ይበልጥ የምናጠናክርበት ሊሆን ይገባል ብለዋል።   ኢሬቻ የሰላም፡ የፍቅር፡ የመቻቻልና የይቅርታ በዓል መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ሌላው ከኦሮሚያ ክልል የመጡት አባ ገዳ ሃይሉ ለገሰ ናቸው። የኢሬቻ በዓል የክረምቱ ወራት መውጫን ተከትሎ ለፈጣሪ ምስጋና የሚቀርብበት መሆኑን ጠቅሰው፤ በዓሉን ስናከብር አንድነታችንን በማጎልበትና ለሰላማችን ዘብ በመቆም ሊሆን ይገባል ብለዋል። የመልካ ባሮ ኢሬቻ በዓል በጋምቤላ ትናንት በፓናል ውይይት የተከበረ ሲሆን ዛሬ ደግሞ በባሮ ወንዝ በድምቀት በመከበር ላይ ይገኛል።
የስነምግባር መምህሩና የብዝሃ ሕይወት ተንከባካቢው የአባ መፍቀሬ ስብዕ ኪዳነወልድ የቀብር ስነ-ስርዓት ተፈፀመ
Oct 19, 2024 135
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 9/2017(ኢዜአ)፦ የስነምግባር መምህሩና የብዝሃ ሕይወት ተንከባካቢው የአባ መፍቀሬ ስብዕ ኪዳነወልድ የቀብር ስነ-ስርዓት ዛሬ ተፈፅሟል። አባ መፍቀሬ ሰብዕ ኪዳነ ወልድ በ1921 ዓ.ም ሰሜን ሸዋ ተጉለት ወርቅጉር ተብሎ በሚጠራው አካባቢ አለቃ ወርቅ አገኘሁ አገር ገዳምዬ ሚካኤል፣ ድንቡይ ጊዮርጊስ እንደተወለዱ የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል። በልጅነታቸው በገዳምዬ ሚካኤል ለዲቁና የሚያበቃቸውን ትምህርት ከተማሩ በኋላ ከግብፃዊው ጳጳስ አቡነ ቄርሎስ እጅ ድቁናን ተቀብለው በአካባቢያቸው ባሉ አብያተ ክርስቲያናት እስከ 14 ዓመታቸው ድረስ ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡ በተለያዩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አድባራት በኃማኖታዊ አስተምህሮ አንድነትን በማስተማር እንዲሁም በብዝኻ ሕይወት እንክብካቤና ጥበቃ ከ70 ዓመት በላይ እንደሰሩም ይነገራል፡፡ በዚህም በደሴና አካባቢው እንዲሁም በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ የተለያዩ የኃይማኖት ተከታዮችና የኅብረተሰብ ክፍሎች ዘንድ በእጅጉ ተወዳጅነትን ያተረፉ ታላቅ አባት ነበሩ። አባ መፍቀሬ ስብዕ ኪዳነወልድ ከበርካታ ዓመታት አገልግሎታቸው በኃላ በ96 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም ድካም አርፈዋል። የቀብር ስነ-ስርዓታቸውም የደሴና አካባቢው የተለያዩ እምነት ተከታዮች በተገኙበት በሐይቅ ቅዱስ እስጢፋኖስ እና አቡነ ኢየሱስ ሞአ አንድነት ገዳም ዛሬ መፈጸሙን ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የባቦጋያ ማሪታይምና ሎጀስቲክስ አካዳሚ የሥልጠና መስኩን ለማስፋት እየሰራ ነው
Oct 19, 2024 125
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 9/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ የባቦጋያ ማሪታይምና ሎጀስቲክስ አካዳሚ በማሪታይም ዘርፍ የሚሰጠውን የሥልጠና መስክ ለማስፋት እየሰራ መሆኑን ገለጸ። የአካዳሚው ዲን ቺፍ ቴዎድሮስ ሚሊዮን፤ አካዳሚው የኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ የራሱን የባህር ሰራተኞች በራስ አቅም ለማሰልጠን ታስቦ እንደተቋቋመ ጠቁመዋል። አካዳሚው ላለፉት አስር ዓመታት ለመርከብ ሰራተኞች የማሪታይምና ሎጂስቲክስ እንዲሁም ለባህር ጠላቂዎችና ዋናተኞች የተለያዩ ሥልጠናዎችን ሲሰጥ መቆየቱን ጠቁመዋል።   በተጨማሪም በሎጂስቲክስ ዘርፉ አጫጭር ሥልጠናዎችን እየሰጠ መሆኑን ጠቅሰዋል። እስካሁን ባለው በማሪታይምና ሎጂስቲክስ ዘርፍ እንዲሁም ተያያዥ ዘርፎች ከ9 ሺህ 500 በላይ ባለሙያዎችን አሰልጥኖ ማስመረቁንም ገልጸዋል። ተቋሙ ያሰለጠናቸው ባለሙያዎች በአገር ውስጥና በተለያዩ ዓለም አቀፍ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ድርጅቶች ውስጥ ተሰማርተው እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚከናወነው ንግድ ውስጥ ከ80 በመቶ በላይ በመርከብ መሆኑ ገልፀው ተቋሙ መርከብ ላይ የሚሰሩ ባለሙያዎችን በማሰልጠንና በማብቃት ለዘርፉ እድገት የራሱን አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይ ደግሞ ተማሪዎችን በዘርፉ በተለያዩ መስኮች በተለይም በኢንጅነሪንግና በኖቲካል ሳይንስ ኦፊሰሮችን አስተምሮ ለማስመረቅ እንቅስቃሴ መጀመሩ አንስተዋል። በሌላ በኩል መርከበኞችን በብዛትና በስፋት ለማሰልጠን እንዲቻል የተለያዩ ትብብሮች ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከሚሰሩ የዘርፉ የሥልጠና ተቋማት ጋር ሥምምነቶች መደረጋቸውን አንስተዋል። እነዚህ ትብብሮች ከአካዳሚው ሰልጥነው የሚወጡ ተማሪዎችን የሥራ እድል ከመፍጠር አንፃርም ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳላቸው ገልፀዋል።
የኢሬቻ በዓል  ተከባብሮና ተቻችሎ አብሮ የመኖር እሴትን  እንደሚያጠናክር ተገለጸ 
Oct 19, 2024 105
ጋምቤላ፤ ጥቅምት 9/ 2017 (ኢዜአ)፡- የኢሬቻ በዓል ተከባብሮና ተቻችሎ አብሮ የመኖር እሴትን ይበልጥ የሚያጠናክር መሆኑን የጋምቤላ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር )ገለጹ። ''ኢሬቻ የአንድነት ፣ የወንድማማችነት እና የሰላም መገለጫ ነው'' በሚል መሪ ሀሳብ የመልካ ባሮ ኢሬቻ በዓል በጋምቤላ ከተማ በፖናል ውይይት ዛሬ መከበር ጀምሯል። የባሮ መልካ ኢሬቻ በዓል በአባ መልካ እና በአባ ገዳዎች ምርቃትና መልካም ምኞት በይፋ ተጀምሯል ። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በፖናል ውይይቱ መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት፤ ኢሬቻ የምስጋና፣ የሰላም፣ የይቅርታ፣ የአብሮነትና፣ ወንድማማችነት ና የአንድነት ትስስር የበለጠ የሚጠናከርበት በዓል ነውል። የኢሬቻ በዓል ባህላዊ እሴቱ ተጠብቆ ለትውልዱ እንዲተላለፍ ማድረግ ከዚህ ትውልድ የሚጠበቅ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ ወጣቱ ትውልድ የገዳ ሥርዓት አካል የሆነውን የኢሬቻ በዓል ሳይበረዝ ጠብቆ በማቆየቱ ረገድ ሚናቸው የጎላ ሊሆን እንደሚገባ ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ተናገረዋል። የኦሮሚያ፣ የጋምቤላ እና ቤኒሻንጉል የጋራ ልማት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍሮምሳ ሰለሞን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያውያን በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስክ ተሳስረው የቆዩ ወንድማማች ህዝቦች ናቸው። የመልካ ባሮ ኢሬቻ በዓል በጋምቤላ ከተማ ሲከበር አንድነቱን እና አብሮነቱን የበለጠ በሚያጠናክር መልኩ መሆን እንዳለበትም ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያን በጋራ የሚያከብሩት የኢሬቻ በዓል ባህላዊ እሴቱ እንዲጠበቅና የበለጠ እንዲተዋወቅ ሁሉም ዜጋ ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። የጋምቤላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሳይመን ሙን (ዶ/ር) በበኩላቸው እንደገለጹት፤ የኢሬቻ በዓል አንድነትና አብሮነት የሚያጠናክር ነው። በዓሉን ስናከብር ከሌሎች ወንድምና እህት ህዝቦች ጋር ፍቅርን ፣ አንድነትና መተሳሰብን ይበልጥ የምናጠናክርበት ሊሆን እንደሚገባ አመላክተዋል። ዛሬ በጋምቤላ ከተማ በተጀመረው የመልካ ባሮ ኢሬቻ በዓል አባ ገዳዎች፣ ሃደ ሲንቄዎችና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በፓናል ውይይቱ ላይ ተሳትፈዋል። በዓሉ በነገው ዕለትም በመልካ ባሮ በተለያዩ ባህላዊ ክወኔዎች በድምቀት እንደሚከበርም የተዘጋጀው የድርጊት መርሃ ግብር ያመላክታል።  
ተመራቂዎች በቀሰሙት ዕውቀትና ክህሎት ስራ ፈጣሪ ለመሆን መትጋት አለባቸው - ከንቲባ ከድር ጁሃር
Oct 19, 2024 109
ድሬዳዋ፤ ጥቅምት 9/2017(ኢዜአ)፡- ተመራቂዎች በቀሰሙት ዕውቀትና ክህሎት ስራ ፈጣሪ ሆነው ከራሳቸው አልፈው ሀገራቸውን ለመጥቀም መትጋት እንዳለባቸው የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር አስገነዘቡ። የድሬዳዋ ፖሊ ቴክኒክ እና የኢትዮ-ጣሊያን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጆች 681 ተማሪዎችን ዛሬ አስመርቀዋል።   በጤና፣ በኤሌክትሪካል ቴክኖሎጂ፣ በአካውንቲንግና ፋይናንስ፣ በአይሲቲ፣ በአውቶሞቲቭ በማኑፋክቸሪንግ፣ በሆቴልና ቱሪዝም እንዲሁም በሌሎች የሙያ ዘርፎች የሰለጠኑ መሆናቸው ተገልጿል። ከተመራቂዎቹ መካከል 447 ሴቶች መሆናቸውም ተጠቅሷል። በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የተገኙት የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት ላመጡ ተመራቂዎች የተዘጋጀውን ሽልማት ከሰጡ በኋላ መልዕክት አስተላልፈዋል። በመልዕክታቸውም መንግስት ለሀገር ሁለንተናዊ ዕድገት ከፍተኛ ሚና ለሚጫወተው ለትምህርትና ስልጠና ዘርፍ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይ ችግር ፈቺ፣ ብቁ እና ተወዳዳሪ ዜጎችን በማፍራት ረገድ ዓይነተኛ ሚና እየተጫወተ የሚገኘውን ቴክኒክና ሙያ ዘርፎችን ለአብነት በመጥቀስ። ዛሬ በተለያዩ የሙያ መስኮች የተመረቁት ዜጎች በቀሰሙት ክህሎትና ዕውቀት በመታገዝ ስራ ፈጣሪ እና ተመራማሪ በመሆን የማህበረሰቡን ችግሮች ማቃለል ይገባቸዋል ብለዋል። ስራን መጠበቅ ሳይሆን በቀሰሙት ክህሎትና ዕውቀት በመታገዝ ከራሳቸው አልፎ ሀገራቸውን ለመጥቀም መትጋት አንዳለባቸው አሳስበዋል። ተመራቂዎቹ በቆይታቸው ራሳቸውንና ሀገራቸውን መለወጥ የሚያስችላቸውን ዕውቀትና ክህሎት መቅሰማቸው ተመልክቷል። በቀንና በማታ መርሃግብር ሙያዊ ዕውቀትና ክህሎት ቀስመው የተመረቁት ተማሪዎች በአስተዳደሩ ከሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎች ጋር በመተሳሰር የራሳቸውን ስራ መጀመራቸውን የገለጹት የኢትዮ-ጣሊያን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዲን አቶ ታደለ አሰፋ ናቸው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የዕለቱ ተመራቂዎች እንደተናገሩት፤ የቀሰሙት ዕውቀትና ክህሎት በግልና በጋራ ስራ ፈጥረው ለመስራት የሚያስችላቸው ነው። ከተመራቂዎቹ መካከል ረመዳን ደስታ፤ ከወዲሁ ተደራጅተው የራሳቸውን የፈጠራ ውጤቶች ለአምራች ኢንዱስትሪዎች ማቅረብ መጀመራቸውን ተናግሯል። በምረቃው ሥነ-ሥርዓት የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ፈትህያ አደንን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ አመራር አባላትና የተመራቂ ቤተሰቦች ተገኝተዋል።
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የአብሮነትና የመደጋገፍ ባህልን እያጎለበተ መሆኑ ተገለጸ
Oct 19, 2024 77
ባህር ዳር ፤ ጥቅምት 9/2017(ኢዜአ)፦ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የእርስ በእርስ የመደጋገፍ ባህልን በማጎልበት አንድነትን ያጠናክራል ሲሉ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪና የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ሙሉነሽ ደሴ ገለፁ። የክረምት በጎ ፈቃድ ማጠናቀቂያና የበጋ በጎ ፈቃድ ማስጀመሪያ እንዲሁም ለውጤታማ አትሌቶች ሽልማት መርሃ ግብር ዛሬ በባህር ዳር ከተማ ተካሄዷል።   የቢሮ ሃላፊዋ ሙሉነሽ ደሴ (ዶክተር) እንደገለጹት፤ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የመንግስትን የልማት ክፍተት በመሙላት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። ወጣቶችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች በየዓመቱ በክረምት ወቅት በሚያካሄዱት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባር አቅመ ደካሞች የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ገልጸዋል። ''በጎ ፈቃድ አገልግሎት በሃሳብ፣ በጉልበትና በገንዘብ ለሌሎች አስተዋጽኦ ማበርከት ነው'' ያሉት ሃላፊዋ መስጠት ደግሞ ከሚያስደስቱና የአእምሮ እርካታ ከሚፈጥሩ ነገሮች ዋናው እንደሆነ ተናግረዋል። አረጋዊያንን በመደገፍ፣ ህፃናትን በማስተማር፣ ምድርን በአረንጓዴ በማልበስ፣ ደም በመለገስ የእናቶችን ሕይወት በመታደግና ሌሎች ተግባራትን በማከናወን የተገኘው ውጤት የእርስ በእርስ የመረዳዳት ባህልን በማጎልበት የአብሮነት ባህልን የበለጠ የሚያሳድግ እንደሆነም ገልፀዋል። ይህ ተግባር በክረምት ብቻ የሚከወን ሳይሆን በበጋ ወራትም ጭምር በማካሄድ የህብረተሰቡ የዘወትር ተግባር ማድረግ በየደረጃው ያለው አመራር አባላትና ወጣቶች ሃላፊነት መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። የአገራችን ሰንደቅ ዓላማ በዓለም አደባባይ ከፍ ብሎ እንዲውለበለብ ላደረጉት የክልሉ እትሌቶችም ኮርተንባችኋል ነገም ታኮሩናላችሁ በማለት ምስጋና አቅርበውላቸዋል።   የአማራ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ሃላፊ አቶ እርዚቅ ኢሳ በበኩላቸው፤ የዛሬው መርሃ ግብር በበጎ ፈቃድ ስራ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱና ለአትሌቶቻችን እውቅና የምንሰጥበት ነው ብለዋል። ''በጎነትና አብሮነት ለኢትዮጵያ ከፍታ'' በሚል መሪ ሃሳብ በተካሄደው የክረምቱ በጎ ፈቃድ ስራ ከስድስት ነጥብ ሶስት ሚሊዮን በላይ ህዝብ በማሳተፍ ከ16 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ይህን መልካም ተግባር በበጋው ወቅትም በማስቀጠል አቅመ ደካሞች ያለባቸውን ችግር ማቃለል እንደሚገባ ጠቁመው፤ ለዚህም የወረዳ፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራሮች ታላቅ ሃላፊነት እንዳለባቸው ተናግረዋል።   በዕለቱም በ2024 የፓሪስ ኦሎምፒክና ሌሎች የውድድሮች ሜዳሊያ ላስመዘገቡ አትሌቶች፣ አሯሯጮችና አሰልጣኞች የገንዘብ ሽልማትና እውቅና ተሰጥቷል። በባህር ዳር ከተማ በተካሄደው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ የእውቅናና ሽልማት መርሃ ግብርም የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራሮችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
ዩኒቨርሲቲዎች ችግር ፈቺ የጥናትና ምርምር ስራዎችን እንዲያከናወኑ ድጋፍና ክተትል እየተደረገ ነው
Oct 19, 2024 104
ደሴ ፤ ጥቅምት 9/2017(ኢዜአ)፦ የዩኒቨርሲቲዎች ጥናትና ምርምሮች ወጪ ቆጣቢና የህብረተሰቡን ችግር የሚፈቱ ሆነው እንዲከናወኑ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተገለጸ። በወሎ ዩኒቨርሲቲ በ"ጭብጥ" ተኮር ጥናትና ምርምር ዙሪያ የውይይት መድረክ ተካሂዷል።   በትምህርት ሚኒስቴር የምርምርና ማህበረሰብ ጉድኝት መሪ ሥራ አስፈጻሚ ሰራዊት ሀንድሰው (ዶ/ር) እንደገለፁት፤ ዩኒቨርሲቲዎች አገር በቀል እውቀቶችን በመጠቀም በፈጠራና ምርምር፣ ቴክኖሎጂ ሽግግር፣ አተኩረው በመስራት አገርና ህዝብ ማገልገል ይጠበቅባቸዋል። በዩኒቨርስቲዎች ከፍተኛ ገንዘብና እውቀት ፈሶባቸው የሚከናወኑ የጥናትና ምርምር ስራዎች የህብረተሰቡን የዕለት ከዕለት ችግር በማቃለል ተጠቃሚነቱን ሊያሳድጉ የሚችሉ መሆን እንዳለባቸው አመልክተዋል። ለዚህም ሚኒስቴሩ እውቀት መር ችግር ፈች ጥናትና ምርምር እንዲካሄድ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ለተግባራዊነቱም የተጠናከረ ክትትልና ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ለዚህም ይረዳ ዘንድ ዘንድሮ መተግበር የሚጀምር "ጭብጥ ተኮር" ምርምር /thematic research/ አሰራር መዘርጋቱን ገልፀው፤ "መመሪያ፣ ደንቦችና አሰራሮች ተዘጋጅተው እየተተገበሩ ነው" ብለዋል። "ጭብጥ ተኮር" ጥናትና ምርምር ተመራማሪዎች ከተናጠል ይልቅ አቅማቸውንና ክህሎታቸውን አሰባስበው እንዲመራመሩና መፍትሔ እንዲያመነጩ ከማድረግ ባለፈ ሀብትን፣ ጉልበትንና ጊዜንም እንደሚቆጥብ ተናግረዋል። ቀደም ሲል የሚሰሩ ጥናትና ምርምሮች ችግር ፈች ካለመሆናቸውም በላይ በድግግሞሽ ሀብትም ያለ አግባብ ይባክን እንደነበር አስታውሰው፤ "አሁን ይህን ችግር በሚፈታ አግባብ ይተገበራል" ብለዋል። በዩኒቨርሲቲዎች ነባራዊ ሁኔታውን ታሳቢ በማድረግ በቱሪዝም፣ ትምህርት፣ ጤና፣ ቴክኖሎጂና ግብርና ዘርፎች ላይ በትብብርና በቅንጅት እንዲሰሩ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጠርም ተናግረዋል። የወሎ ዩኒቨርስቲ ምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሰይድ ሁሴን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በ"ጭብጥ ተኮር" ጥናትና ምርምርን ከሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በትብብር እንደሚሰራ ገልጸዋል።   ተመራማሪዎች የህብረተሰቡን ችግር በጋራ ለይተውና የመፍትሔ ሀሳብ አመንጭተው በዘላቂነት መፍታት የሚችል አውድም እንደሚፈጠር ገልጸዋል። ''ጭብጥ ተኮር" ጥናትና ምርምር በአገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ከሌሎች ተመራማሪዎች ጋር ጥልቅ ምርምር ለማድረግ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ነው'' ያሉት ደግሞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የእጽዋት ሳይንስና ብዝሃ ሕይወት መምህርና ተመራማሪ ፕሮፌሰር ማስረሻ ፈጠነ ናቸው።   እስካሁን በተናጠል የተከናወኑ ጥናቶች በሚፈለገው ልክ የህብረተሰቡን ችግር ካለመፍታቱና በአንድ ርዕሰ ጉዳይ ተደጋጋሚ ጥናት ከማድረግ ባለፈ ጊዜ፣ ጉልበትና ሀብት ሲያባክን መቆየቱን ገልጸዋል። በውይይት መድረኩ የዩኒቨርሲቲ አመራር አባላት፣ ተመራማሪዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል።
ወሎ ዩኒቨርሲቲ በልዩ ልዩ የትምህርት ዘርፎች ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች አስመረቀ
Oct 19, 2024 79
ደሴ ጥቅምት 9/2017(ኢዜአ)፦ ወሎ ዩኒቨርሲቲ በልዩ ልዩ የትምህርት መርሃ ግብሮች በመጀመሪያና በሁለተኛ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን 2 ሺህ 224 ተማሪዎች ዛሬ አስመርቋል። ዩኒቨርሲቲው ዛሬ ያስመረቃቸው በመደበኛ፣ በክረምትና በተከታታይ የትምህርት መርሃ ግብሮች ትምህርት ሲከታተሉ የቆዩ 2 ሺህ 224 ተማሪዎችን ነው። የወሎ ዩኒቨርሲቲ ተወካይ ፕሬዚዳንት ዶክተር አወል ሰይድ እንደገለጹት፤ ምሩቃን ውስብስብ ችግሮችን አልፈው ለዛሬ መብቃታቸው ለዓላማ አይበገሬነታቸውን ያሳየ በመሆኑ ስራ ፈጣሪ እንጂ ስራ ጠባቂ መሆን አይገባቸውም። ከተጠቀሱት ተማሪዎች ውስጥም 256ቱ በሁለተኛ ዲግሪ ቀሪዎቹ ደግሞ በመጀመሪያ ዲግሪ የተመረቁ ሲሆን፤ ከአጠቃላይ ተመራቂ ተማሪዎች 568 የሚሆኑት ሴቶች መሆናቸውን ገልፀዋል።   ተመራቂዎቹ በኮምፒዩተር ሳይንስ፣ በምህንድስና፣ በቢዝነስና ኢኮኖሚክስ እንዲሁም በግብርናና መሰል የትምህርት ዘርፎች ትምህርታቸውን ሲከታተሉ መቆየታቸውንም አስረድተዋል። የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ መሀመድ አሚን የሱፍ በበኩላቸው፤ መማር ከሌሎች በተሻለ ለህዝብ አገልግሎትና ለአገር እድገት ልቆ መገኘት መሆኑን ተናግረዋል። ለዚህም ምሩቃን በቆይታቸው ያገኙትን እውቀትና ክህሎት ተጠቅመው ህብረተሰቡን በቅንነትና በታማኝነት ማገልገል እንዳለባቸው አመልክተዋል። ''እንዲሁም አገር በዘላቂነት የምትገነባው በተማረ የሰው ሃይል መሆኑን በመገንዝብ ተማሪዎች ለአገራችን ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና አንድነት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ ቀን ከሌት ሊሰሩ ይገባል" ሲሉም አስገንዝበዋል። በሰለጠነችበት የኮምፒውተር ሳይንስ ትምህርት ዕውቀት የራሷን ስራ በራሷ አቅም ለማመቻቸት እቅድና ተነሳሽነት እንዳላት የገለፀችው ደግሞ ሰዓዳ አህመድ ናት። ዩኒቨርሲቲው በአሁኑ ወቅት ከ21 ሺህ በላይ ተማሪዎችን እያስተማረ እንደሚገኝም ታውቋል። በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ የዩኒቨርስቲው ማህበረሰብ አባላት፣ የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር አመራር አባላትና የተመራቂ ተማሪዎች ቤተሰቦች ተገኝተዋል።
ፍትኃዊና ቀልጣፋ የዳኝነት አገልግሎት ለመስጠት በቴክኖሎጂ የተደገፉ አሠራሮች ተጠናክረው ይቀጥላሉ 
Oct 19, 2024 81
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 9/2017(ኢዜአ)፦ ፍትኃዊና ቀልጣፋ የዳኝነት አገልግሎት ለመስጠት በቴክኖሎጂ የተደገፉ አሠራሮች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ገለጸ። የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የተጠናቀቀው 2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2017 ዓ.ም የትኩረት አቅጣጫ በተመለከተ ከዘርፉ ተዋናዮች ጋር ምክክር አድርጓል። በምክክር መድረኩም የባለፈው በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጻም በተመለከተ እንዲሁም የተቋሙን አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ትኩረት ያደረጉ የመወያያ ጽሑፎች ቀርበው ምክክር ተደርጎባቸዋል። የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ሌሊሴ ደሳለኝ በተጠናቀቀው 2016 በጀት ዓመት የከፍተኛ ፍርድ ቤቶችን የዳኝነት አገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን ለኅብረተሰቡ ተገቢውን አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ ተግባራቶች የተከናወኑበት እንደነበር አስታውሰዋል። ከእነዚህም ውስጥ የተለያዩ ሪፎርም ሥራዎችን ማከናወን፣ አሠራሮችን በቴክኖሎጂ የተደገፉ እንዲሆኑ ማድረግ፣ የባለሙያን አቅም ማሳደግ ተጠቃሽ መሆኑን ተናግረዋል። የዳኝነት አገልግሎት ለማቀላጠፍ በተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ ተግባራትም በርካታ የወንጀልና የፍትሐብሔር መዝገቦች ላይ ተገቢውን ውሳኔ እንዲሰጥ በማድረግ አበረታች ሥራ መሰራቱን ገልፀዋል። በዚህም መሠረት በ2016 ዓ.ም 20 ሺህ 784 የወንጀልና ፍትሐብሔር መዝገቦች ላይ ውሳኔ ለመስጠት ታቅዶ 24 ሺህ 853 መዛግብቶች ላይ የዳኝነት ውሳኔ ተሰጥቷል ብለዋል። ከዚህም ባሻገር ፍርድ ቤቱ የዘገዩ ውዝፍ መዛግብቶች የመለየት ሥራ በማከናወን ዳኞች የመደበኛ ሥራ ጊዜያቸው ዝግ በሆነበት ጊዜ ያላቸውን የእረፍት ጊዜ በመጠቀም በነሐሴና በመስከረም ላይ 2 ሺህ 485 የሚሆኑ መዛግብት መፍትሔ እንዲያገኙ ተደርጓል ነው ያሉት። የዳኝነት አገልግሎት ተደራሽነትን ብሎም የአሠራር ጥራትን ቀጣይነት ባለው መልኩ ለማስኬድ በቴክኖሎጂ የተደገፈ ሥራ መሥራት የሚጠይቅ መሆኑን ጠቁመዋል። አሁን ባለንበት በጀት ዓመት ፍትሕ ለሚሹ ዜጎች ተገቢውን አገልግሎት ለመስጠት ዳኞች ነፃና ገለልተኛ በሆነ መልኩ ሥራቸውን የሚያከናውኑበት ምቹ ሁኔታን የመፍጠር ሥራ ፍርድ ቤቱ ትኩረት አድርጎ እየሰራ እንደሚገኝ ገልፀዋል። በተመሳሳይ ዜጎች ፍትኃዊና ቀልጣፋ የሆነ የዳኝነት አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግ የተጀመሩ በቴክኖሎጂ የተደገፉ አሠራሮች ላይ ልዩ ትኩረት በመስጠት እየተሰራበት መሆኑን ተናግረዋል።   በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት የዕቅድ ዝግጅት ክትትልና ግምገማ ዳይሬክተር ሶፋኒት አየለ በበኩላቸው፤ ፍርድ ቤቱ ሕብረተሰቡ በተቀላጠፈ መልኩ የዳኝነት አገልግሎትን እንዲያገኙ ለማስቻል የአንድ መስኮት አገልግሎት ለማስፋት እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በተጨማሪም የዘመኑ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ተገልጋዮች የፍትሕ አገልግሎትን ለማግኘት የሚጠቅማቸውን መረጃዎች በዲጂታል ሥርዓት የማስደገፍ ሥራ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በመድረኩም የዳኝነት ውሳኔ እንዲዘገዩ ከሚያደርጉ ተግዳሮቶች መካከል በድምፅ የተቀዱ መረጃዎችን ወደ ጽሑፍ የመቀየር ሥራ ተጠቃሽ መሆኑ ተጠቁሟል። ይህንንም ችግር ለመቅረፍ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ድምፅን ወደ ጽሑፍ ለመቀየር የሚያስችል ሶፍትዌር አሁን ላይ ምቹ ማድረግ መቻሉን ዳይሬክተሯ ገልፀዋል።  
የቃሊቲ መናኸሪያ በቅርቡ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ይሆናል
Oct 19, 2024 75
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 9/2017(ኢዜአ)፦ ለተገልጋይ ምቹ በሆነ አግባብ የተገነባው የቃሊቲ መናኸሪያ በቅርቡ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚሆን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር ገለፀ። የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት አምባሳደር ታዬ አፅቀ ሥላሴ ለሁለቱ ፓርላማ የፌደራል መንግሥቱን ዓመታዊ ዕቅድ ባቀረቡበት ወቅት በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ ሥራዎች አበረታች ውጤት መመዝገባቸን መግለፃቸው ይታወቃል። ፕሬዝዳንቱ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መሠረተ-ልማትን ለማስፋፋት በተሰሩ ሥራዎች በየብስ፣ በአየር ትራንስፖርት እንዲሁም በባህር ትራንስፖርት ዘርፍ በየዓመቱ አበረታች ውጤት እየተመዘገቡ መሆኑንም ተናግረዋል። መናኸሪያዎችን ማስፋፋት፣ አሠራራቸውን ማቀላጠፍና ማዘመን በየዓመቱ ከተሰሩ ሥራዎችና ውጤት ከተመዘገበባቸው መካከል እንደሆኑ መጥቀሳቸውም እንዲሁ። ይህንንም ተከትሎ ከ2011 ዓ.ም ተጀምሮ በተለያዩ ምክንያቶች ተጓቶ የነበረው የቃሊቲ መናኸሪያ ግንባታም በተያዘው ዓመት ተጠናቆ በቅርቡ እንደሚመረቅ ተገልጿል። በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር የቃሊቲ መናኸሪያ ግንባታ ፕሮጀክት ባለቤት መሐንዲስ ሚኪያስ ታደሰ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የቃሊቲ መናኸሪያ ከዚህ በፊት ይሰጥ የነበረው አገልግሎት ለተጓዞች ምቹ አልነበረም። የመናኸሪያውን አገልግሎት ለተገልጋዮች ምቹና ዘመናዊ ለማድረግ በርካታ አገልግሎቶችን መስጠት የሚያስችል ባለአራት ወለል ሕንፃን ያካተተ ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ለተለያዩ አገልግሎት የሚውሉ በርካታ ቢሮዎችና ሱቆችን እንዲሁም የስብሰባ አዳራሽን ያካተተውን ሕንፃ ጨምሮ 120 አውቶቡሶችን ማስተናገድ የሚችል ሥፍራን ያካተተ እንደሆነም ገልፀዋል። የመናኸሪያ ግንባታው 1 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር የፈጀ መሆኑን ጠቁመው፤ ተገልጋዮች ዘመናዊ አገልግሎት ማግኘት እንዲችሉ ተደርጎ መገንባቱንም አስረድተዋል። በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር የመሠረተ-ልማት መሪ ሥራ አስፈጻሚ ሰይፉ ክንፉ በበኩላቸው፤ የሕዝብ ትራንስፖርት የሚሰጥባቸው ቦታዎች ላይ ዜጎች ሳይጉላሉ እንዲንቀሳቀሱ ለማድረግ አገልግሎቱን ምቹ የማድረግ ሥራ እየተሰራ ነው ብለዋል።   መናኸሪያው ለተጓዦች የተለያዩ አገልግሎቶችን ለመስጠት እንዲያስችል ተደርጎ መገንባቱን ገልፀዋል። የቃሊቲ መናኸሪያ ዘመናዊና በቴክኖሎጂ የተደገፈ በማድረግ ሁሉን አቀፍ አገልግሎት መስጠት በሚያስችል መልኩ መገንባቱን ጠቁመው፤ የግንባታው አፈጻጸም አሁን ላይ ከ95 በመቶ በላይ መድረሱን ተናግረዋል። መናኸሪያው በቅርቡ ተጠናቆ ለኅብረተሰቡ አገልግሎት እንደሚሰጥም ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም