ቀጥታ፡
ማህበራዊ
በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል የተጀመሩ ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል   
Oct 13, 2025 47
ወራቤ ፤ጥቅምት 3/2018(ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል የተጀመሩ ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የክልሉ ትምህርት ቢሮ ገለፀ፡፡ ቢሮው "የትምህርት ጥራት ለሁለንተናዊ ብልፅግና" በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጀው 2ኛው የትምህርት ጉባኤ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በተገኙበት በወራቤ ከተማ እያካሄደ ነው፡፡   የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ፋጤ ስርሞሎ፣ የኢፌዴሪ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ አየለች እሸቴን ጨምሮ ሌሎች የመንግስት የስራ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት በመሳተፍ ላይ ናቸው፡፡ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፈቃዱ እንዳሉት፡በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል የተጀመሩ ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል።   በዚህም በ2017 የትምህርት ዘመን በትምህርት ለትውልድ ንቅናቄ ማህበረሰቡን በማሳተፍ 78 አዳዲስ ትምህርት ቤቶችን የማሰራትና 691 ተጨማሪ የመማሪያ ክፍሎችን የመገንባት ስራ ተሰርቶ ለአገልግሎት መብቃታቸውን ተናግረዋል፡፡ የተማሪዎችን መጠነ ማቋረጥ ለመቀነስም ከ118 ሺህ በላይ ተማሪዎች የትምህርት ቤት ምገባ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡ በዚህም የተማሪዎች ውጤት እየተሻሻለ መምጣቱን አንስተው ተግባሩን ለማጠናከር ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡ የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘይኔ ቢልካ በበኩላቸው፤በዞኑ ለትምህርት ዘርፉ የተሰጠውን ትኩረት ውጤታማ ለማድረግ ማህበረሰቡን ያሳተፈ ተግባር በመከናወን ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡   በ2017 የትምህርት ዘመን የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ለማሻሻልና ለመፃህፍት ህትመት የሚሆን ከ376 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ በማሰባሰብ የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ማሻሻል መቻሉን ጠቁመዋል፡፡ እንዲሁም በአዲሱ ፍኖተ ካርታ የተዘጋጀውን የተማሪዎች መፃህፍት በማሳተም ለተማሪዎች ማሰራጨት መቻሉን ጠቅሰው በዚህም ተስፋ ሰጪ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝም ገልፀዋል፡፡ በጉባኤውም በክልሉ በትምህርት ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትና የቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ውይይት እንደሚደረግም ተመላክቷል፡፡
እየተስፋፋ የመጣውን እና አሳሳቢውን የኩላሊት መድከም እንዴት መከላከል ይቻላል?
Oct 13, 2025 97
ለኩላሊት ህመም አጋላጭ መንስዔዎችን በአግባቡ ማወቅ እና ከእነዚህ ሁኔታዎች መራቅ አስፈላጊ ነው። ስኳርና ደም ግፊትን ጨምሮ በኩላሊት ላይ ጫና የሚያሳድሩ የተለያዩ ህመሞች ያሉበት ሰው ተገቢውን ክትትልና ሕክምና ማድረግ ይጠበቅበታል። የደም ማነስ፣ የሰውነት ድካም፣ የቆዳ ድርቀትና ማሳከክ፣ የምግብ ፍላጎት ማጣትና ማቅለሽለሽ፣ የሰውነት ዕብጠት፣ የሽንት መጠን መቀነስ ሲስተዋል ቶሎ ተገቢውን ሕክምና ማድረግ ይመከራል። የመድኃኒት አወሳሰድን ማስተካከልና ኩላሊትን ሊጎዱ የሚችሉ መድኃኒቶችን አለመውሰድ ተገቢ ነው። ከመጠን ያለፈ ውፍረትን ማስወገድ፤ ከደባል ሱሶችም መታቀብ የኩላሊት መድከምን ለመቀነስ ብሎም ለጤናማ ኑሮ ይበጃል። አመጋገብን ማስተካከል (ንጽህናው የተጠበቀ፣ የተመጣጠነ፣ ቤት ውስጥ የተዘጋጀ ምግብ መመገብ) እንደሚገባም የሕክምና ባለሙያዎች ይመክራሉ። ጨው፣ ቅባት፣ የሥጋ ውጤቶች፣ የወተት ተዋጽዖና የታሸጉ ምግቦችን አጠቃቀም መቀነስ አስፈላጊ መሆኑም ይነሳል።
መንግስት ባህላዊ እሴቶች ለምተው ለቱሪስት መስህብና ለሁለንተናዊ ብልፅግና መሰረት እንዲሆኑ አድርጓል
Oct 12, 2025 146
አዲስ አበባ፣ጥቅምት 2/2018 (ኢዜአ)፡-መንግስት ተደብቀው የቆዩ ባህላዊ እሴቶች ለምተው ለቱሪስት መስህብና ለሁለንተናዊ ብልፅግና መሰረት እንዲሆኑ ማድረጉን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እፀገነት መንግስቱ ገለጹ። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ከሌሎች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የአዳብና ፌስቲቫል መዝጊያ መርሃግብር ተካሂዷል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ከፍተኛ የፌዴራልና የክልል የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣የሀገር ሽማግሌዎች፣ የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣የአካባቢው ተወላጆችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እፀገነት መንግስቱ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ፤ኢትዮጵያ አኩሪ የሆነ ብዝሃ ባህል ያላት አገር ናት። ከለውጡ በኃላ አቧራ ለብሰው ተሸፍነው የቆዩ ባህሎች እያደጉ የቱሪስት መስህብ እየሆኑ በመምጣት የአገሪቱ ምድረ ቀደምትነት እየተገለፀ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ባህላዊ እሴቶች ለሁለንተናዊ ብልፅግና አስተዋፅኦ እንዲያበረክቱ ማስቻሉን ገልጸዋል። አዳብና ከጊዜ ወደጊዜ እየተረሳ መምጣቱን ጠቁመው፥ መንግስት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ሳይበረዝ ወደቀድሞ ለመመለስ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ የተከበረው የአዳብና በዓል ማህበራዊ መስተጋብርንና በህዝቦች መካከል ያለ ትስስርን የሚያጠናክር ነው ብለዋል። በበዓሉ ለሰላም እሴት ግንባታና በሁሉም ዘርፍ አስተዋፅኦ ያለው በመሆኑ ባህላዊ እሴቱን ጠብቆ እንዲቆይ መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል።   የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነፊሳ አልማህዲ በበኩላቸው፥ አዳብና ለዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታና ማህበረሰብ ግንባታ ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። ሚኒስቴሩ ባህላዊ ስርዓቶች በሚገባ ተጠንተውና ለምተው የአገር ብልፅግና ለማረጋገጥ እንዲውሉ ተገቢውን ድጋፍ ያደርጋል ነው ያሉት። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ምክር ቤት አፈጉባኤ እንዳልካቸው ጌታቸው፥ አዳብና የሶዶ ክስታኔ ዋነኛ መገለጫ ከሆኑት ባህልና እሴቶች መካከል አንዱ መሆኑን ገልፀዋል። አዳብና ከመስከረም 16 እስከ ጥቅምት 5 ድረስ በተለያዩ አካባቢዎች በገበያና ሃይማኖት ቦታዎች የሚካሄድ ነው ያሉት ደግሞ በዞኑ የባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ ብሩክታዊት ፀጋዬ ናቸው። የአክራሜ በጎ አድራጎት ሴቶች ማህበር ሰብሳቢ ሳራ ስዩም በበኩላቸው፥ የአዳብና በዓል የወጣቶች የነፃነትና የመተጫጨት በዓል መሆኑን ተናግረዋል። በዓሉን በሀገርና በዓለም ደረጃ ለማስተዋወቅ ብሎም በዩኔስኮ የማይዳሰስ ቅርስነት ለማስመዝገብ እየተሰራ መሆኑንም ገልፀዋል።
ወሰን ተሻጋሪ የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ለሕብረ ብሔራዊ አንድነት ግንባታ ወሳኝ ሚና አለው
Oct 12, 2025 129
ወልቂጤ፤ጥቅምት 2/2018 (ኢዜአ) ፡-ወሰን ተሻጋሪ የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ሕብረ ብሔራዊ አንድነት የሰፈነባት ጠንካራ ሀገር ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ወሳኝ ሚና እንዳለው የሰላም ሚኒስቴር ገለፀ። የሰላም ሚኒስቴር ለ14ኛ ዙር ያዘጋጀው ብሔራዊ የወጣቶች በጎ ፍቃድ አገልግሎት ስልጠና በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ መሰጠት ተጀምሯል። "በጎነት ለአብሮነት" በሚል መሪ ሀሳብ ዛሬ በተጀመረውና ለአንድ ወር በሚቆየው ስልጠና ከአንድ ሺህ በላይ ወጣቶች በመሳተፍ ላይ ናቸው። በሰላም ሚኒስቴር የሰላም ግንባታ እና ብሔራዊ መግባባት ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ አቶ ፍሬሰንበት ወልደተንሳይ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የወጣቶችን የሀገርና የሕዝብ ፍቅር ለማሳደግ አስተዋጾ እያደረገ ነው። አገልግሎቱ በተለይ ሕብረ ብሔራዊ አንድነት የሰፈነባት ጠንካራ ሀገር ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ወሳኝ ሚና እንዳለውም ተናግረዋል። ዛሬ ለወጣቶች መሰጠት የተጀመረው ስልጠናም ኢትዮጵያዊ እሴቶችንና መርሆችን ለወጣቱ ትውልድ ለማስረጽ ያለው ጠቀሜታ የጎላ መሆኑንም ገልጸዋል። ወጣቶቹ በቀጣይ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በመንቀሳቀስ የሥራ ባህልን በማጎልበት፣ በህይወት ክህሎት፣ መልካም ስነምግባርን በማስረጽና እና በሀገራዊ አንድነት ላይ እንደሚሰሩም አመልክተዋል። በዚህም በህብረተሰቡ ውስጥ አስተሳሳሪ ገዥ ትርክትን በማስረፅ ለሕብረ-ብሔራዊ አንድነትን መጠናከር፣ ለዘላቂ ሠላም ግንባታና ልማት የበኩላቸውን ሚና እንደሚወጡ ተናግረዋል። እንደእሳቸው ገለጻ ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ወንድማማችነትና እህታማማችነትን ለማጎልበት፣ ሌሎች የማህበረሰብ ክፍሎችን ለማወቅና ከአካባቢ ባሻገር ሀገራዊ አስተሳሰብን ለማዳበር ይረዳል፡፡ "ሁሉም ዜጋ ለሰላምና ልማት መረጋገጥ አምባሳደር መሆን አለበት" ያሉት ደግሞ የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የአስተዳደርና ልማት ምክትል ፕሬዚዳንት የሺሀረግ አፈራ (ዶ/ር) ናቸው፡፡ በስልጠናው ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የመጡ ወጣቶች እየተሳተፉ መሆናቸውን ጠቁመው፣ ወጣቶቹ ባህልና እሴቶቻቸውን ለሌሎች በማስተዋወቅ አብሮነትን ለማጠናከር የበኩላቸውን ሊወጡ ይገባል ብለዋል። ዩኒቨርሲቲው በሀገሪቱ ያሉና ለህዝቦች ትስስር ምሶሶ የሆኑ ዕሴቶች እንዲጎለብቱ በመሰነድና ለትውልድ እንዲሸጋገሩ በማድረግ የበኩሉን እየተወጣ መሆኑንም ተናግረዋል። ከስልጠናው ተሳታፊዎች መካከል ወጣት ላእመቾ ፍቅሬ እና ህይወት ኤልያስ ስልጠናው በተለያዩ አካባቢዎች ያሉ እሴቶችን የበለጠ ለመረዳት ከሚሰጠው እድል ባለፈ በህይወት ክህሎት ላይ የተሻለ ዕውቀት የሚያስጨብጥ ነው ብለዋል፡፡ እንደሀገር የተጀመሩ ትልልቅ የልማት ሥራዎችን ለማጠናከር በሰላም፣ በብሔራዊ መግባባትና በአብሮነት ላይ ለመስራት ዝግጁነታቸውን ገልጸዋል፡፡      
ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመከላከል የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ- የጤና ሚኒስቴር
Oct 12, 2025 97
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 2/2018(ኢዜአ)፦መንግሥት ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመከላከል የጀመራቸውን ተግባራት አጠናክሮ እንደሚቀጥል የጤና ሚኒስቴር አስታውቋል። የዓለም የልብ ቀን "አንድም የልብ ምት አታምልጠን" በሚል መሪ ሃሳብ ዛሬ በአዲስ አበባ በተለያዩ ሁነቶች ተከብሯል። በእለቱም የኢትዮጵያ የልብ ማህበር አባላት፣ የህክምና ባለሙያዎችና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ቀኑን ምክንያት በማድረግ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ እና የእግር ጉዞ አካሒደዋል።   ጤና ሚኒስቴርን በመወከል የተገኙት አቶ ሌሊሳ አማኑኤል፤ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት በአሁኑ ወቅት በማሕበረሰቡ ጤና ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሱ ካሉ ችግሮች ዋነኛው ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ናቸው። በዚሁ ሳቢያም መንግስት ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን መከላከል የሚያስችል የጤና ፖሊሲ ተግባራዊ በማድረግ የተጠናከሩ ስራዎችን እየሰራ እንደሚገኝ ገልፀዋል። ከዚህ ውስጥም የባለሙያዎች አቅም በማጠናከር፣ መድሃኒቶች ከውጭ በማስገባት እና የልብ ቀዶ ጥገናዎች በዘመቻ እንዲካሔዱ የማድረግ ተጠቃሽ ስራዎች ናቸው ብለዋል። መንግስት በሽታውን ለመከላከል ከሚያደርገው ጥረት ጎን ለጎን ዜጎች አመጋገባቸውን በማስተካከል እና የአካል ብቃት እንቅስቃሴ በማድረግ ራሳቸውን የመጠበቅ ባሕል ሊያጎለብቱ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።   የኢትዮጵያ የልብ ማኅበር ፕሬዝደንት እንዳለ ገብሬ በበኩላቸው፤ ማህበሩ የዓለም አቀፉ የልብ ቀን ምክንያት በማድረግ የልብ ህክምናዎችን ከመስጠት ባሻገር የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን በመስራት ላይ መሆኑን ተናግረዋል። ከልብ ህመም ጋር ተያይዞ ሕክምና ለማግኝት በርካታ ዜጎች ተራቸውን በመጠባበቅ ላይ በመሆናቸው ይህንኑ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በአሁኑ ወቅትም ከጤና ሚኒስቴር ጋር በመሆን በተለይ በትምህርት ቤቶች የልብ ህመም ጋር ተያይዞ ህክምና የሚፈልጉ ዜጎችን መረጃ የመለየት ስራ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። ማሕበሩ የሕዝብ መድሃኒት ቤቶችን በመክፈት ለረዥም ጊዜ ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ምክንያት መድሃኒት ለሚወስዱ ዜጎች ተደራሽ ለማድረግ እየሰራ እንደሚገኝም አንስተዋል። የልብ ህመም በሕብረተሰቡ ላይ አያስከተለ ያለውን ጉዳት ለመቀነስም በየወቅቱ ምርመራ የማድረግ ባሕልን ማጎልበት እንደሚገባም ነው የጠቀሱት። በመርሀ ግብሩ ላይ የተገኙ ከልብ ህመም ጋር ተያይዞ ህክምና የወሰዱ ታካሚዎች በበኩላቸው፤ማሕበረሰቡ የልብ ህመም የሚያመጡ በሽታዎች ምልክቶችን ሲያይ ፈጥኖ ወደ ሕክምና በመሄድ ህክምና ማድረግ እንደሚገባ ይመክራሉ።   አስተያየት ሰጪዎቹ ወይዘሮ እመቤት አሰሙ እና ወይዘሮ ሚዛን ሀጎስ፤ ልብ ህክምና ከባድና ብዙ ወጪ የሚጠይቅ በመሆኑ አገልግሎት አሰጣጡ ላይ በቅንጅት ቢሰራ አቅም የሌላቸው ዜጎችን ተደራሽ ለማድረግ ያስችላል ነው የሚሉት።    
ኪነ-ጥበብን ለልማትና ለሀገራዊ ትርክት ግንባታ ማዋል ይገባል
Oct 12, 2025 124
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 2/2018 (ኢዜአ)፦ኪነ-ጥበብን ለሀገራዊ ልማትና ትርክት ግንባታ ይበልጥ መጠቀም እንደሚገባ ተገለጸ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት በየወሩ የሚያዘጋጀው የስነ-ጽሁፍ ምሽት "ድህረ ህዳሴ" በሚል መሪ ሀሳብ ተዋቂ ግለሰቦች፣ የኪነጥበብ ባለሙያዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ተከናውኗል፡፡   የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ምክትል ስራ አስፈጻሚ ነጋሲ አምባዬ በወቅቱ፥ ኢትዮጵያ የቁጭት ዘመን አብቅቶ የማንሰራራት ዘመን ላይ እንደምትገኝ ተናግረዋል። ይህንን አዲስ ምዕራፍ በሚገባ ለመግለጽና ለማሳየት የኪነጥበብ ድርሻ ከፍተኛ በመሆኑ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎትም ይህንኑ ለማሳደግ መድረኩ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። ኪነ-ጥበብ የሀገርን ልማት በማፋጠን ሂደት ውስጥ ትልቅና አዎንታዊ ሚና ለማሳደግም ሚዲያ ያለውን አበርክቶ እውን በማድረግ ልማትንና ገጽታ ግንባታን ለማፋጠን እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። አሁን የተዘጋጀው የኪነ-ጥበብ ምሽትም የኢትዮጵያን ከፍታ ለማረጋገጥ ያለመና የጋራ ትርክትን የሚፈጥሩ አጀንዳዎችን ለማንሸራሸር ሚናው የጎላ መሆኑን ጠቁመዋል።   በኪነ-ጥበብ ምሽቱ ላይ የተገኙት የዓባይ ንጉሶች ሚዲያ መስራች ኡስታዝ ጀማል በሽር በበኩላቸው፥ ኢትዮጵያውያን በትብብር ታላቁን የሕዳሴ ግድብ በማጠናቀቅ ታሪክ መሥራታቸውን ገልጸዋል። በዚህ ታሪካዊ ሂደት ውስጥ ኪነ-ጥበቡ ከፍተኛ ሚናውን እንደተጫወተ አንስተዋል። የኪነ-ጥበብ አቅምን በማጎልበት በሕዳሴው ግድብ ያሳየነውን ህብረት በሌሎች የልማት ዘርፎች ላይም መድገም እንደሚገባ ጠቁመዋል። የስነ-ጥበብ ኮሌጅ ዲን አገኘሁ አዳነ፥ ኪነ-ጥበብ በሀገር ግንባታ ያለውን ትልቅ አበርክቶ በመጠቀም ህብረተሰብን ለልማት ማነሳሳት እንደሚገባ ተናግረዋል።   የለውጡ መንግሥት የኪነ-ጥበብ ዘርፍን ለማሳደግ በሰጠው ትኩረት ክዋኔ ጥበባት መድረኮች እንዲስፋፉ ማድረጉን አንስተዋል። ይህም የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች ለሰብዓዊና ለሀገር ልማት የበኩላቸውን አስተዋፅኦ እንዲያደርጉ እድል መፍጠሩን ጠቅሰዋል። በኪነጥበብ ምሽቱ መርሃ ግብር ላይ፣ ከታላቁ የሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ጋር ተያይዘው የተዘጋጁ ግጥሞች፣ መጣጥፎች እና ሌሎች የስነ-ጽሁፍ ስራዎች ቀርበዋል፡፡
የአዳብና የእርስ በርስ መስተጋብርን ለማጠናከርና ለሰላም እሴት ግንባታ አስተዋጽኦ ያለው በዓል ነው
Oct 12, 2025 67
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 2/2018(ኢዜአ)፦የአዳብና በዓል የእርስ በርስ መስተጋብርን ለማጠናከርና ለሰላም እሴት ግንባታ አስተዋጽኦ ያለው በዓል መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እፀገነት መንግስቱ ገለፁ። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ከሌሎች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የአዳብና ፌስቲቫል መዝጊያ መርሃግብር እየተካሄደ ይገኛል።   በመርሃግብሩ ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ ከፍተኛ የፌዴራልና የክልል የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣ የአካባቢው ተወላጆችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እፀገነት መንግስቱ እንዳሉት ኢትዮጵያ አኩሪ የሆነ ብዝሃ ባህል ያላት አገር ናት። ከለውጡ በኃላ አቧራ ለብሰው ተሸፍነው የቆዩ ባህሎች እያደጉ መስህብ እየሆኑ በመምጣት የአገሪቱ ምድረ ቀደምትነት እየተገለፀ መሆኑን ተናግረዋል። አዳብና ከጊዜ ወደጊዜ እየተረሳ መምጣቱንና መንግስት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ሳይበረዝ ወደቀድሞ ለመመለስ እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።   በዓሉ ማህበራዊ መስተጋብርንና በህዝቦች መካከል ያለ ትስስርን የሚያጠናክር ነው ብለዋል። በበዓሉ ለሰላም እሴት ግንባታና በሁሉም ዘርፍ አስተዋፅኦ ያለው በመሆኑ ባህላዊ እሴቱን ጠብቆ እንዲቆይ መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነፊሳ አልማህዲ በበኩላቸው፤ አዳብና ለዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታና ማህበረሰብ ግንባታ ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።   ሚኒስቴሩ ባህላዊ ስርዓቶች በሚገባ ተጠንተውና ለምተው የአገር ብልፅግና ለማረጋገጥ እንዲውሉ ተገቢውን ድጋፍ ያደርጋል ነው ያሉት። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ምክር ቤት አፈጉባኤ እንዳልካቸው ጌታቸው አዳብና የሶዶ ክስታኔ ዋነኛ መገለጫ ከሆኑት ባህልና እሴቶች መካከል አንዱ መሆኑን ገልፀዋል። አዳብና የመተጫጫ፣ የነፃነት እንዲሁም የተጠፋፉ ወዳጆች የሚገናኙበት የወጣቶች እና የልጃገረዶች በዓል ዝግጅት ከመስከረም 16 እስከ ጥቅምት 5 ድረስ በተለያዩ አካባቢዎች በገበያና ሃይማኖት ቦታዎች የሚካሄድ መሆኑን ተናግረዋል። በዓሉን በሀገርና በዓለም ደረጃ ለማስተዋወቅ ብሎም በዩኔስኮ የማይዳሰስ ቅርስነት ለማስመዝገብ እየተሰራ ነው ብለዋል።
ብሔራዊ መግባባትን በመፍጠር ሀገራዊ አንድነት ለማጠናከር በሚደረገው ጥረት የወጣቶች ተሳትፎ ወሳኝ ነው-የሰላም ሚኒስቴር
Oct 12, 2025 72
ደሴ፤ጥቅምት 2/2018 (ኢዜአ)፦ብሔራዊ መግባባትን በመፍጠር ሀገራዊ አንድነት ለማጠናከር በሚደረገው ጥረት የወጣቶች ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን የሰላም ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ 14ኛ ዙር ብሔራዊ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት የሚሰጡ ወጣቶች ስልጠና በወሎ የኒቨርሲቲ አስጀምሯል። በሰላም ሚኒስቴር የሚኒስትሩ አማካሪ አቶ አበበ ወርቁ በስልጠናው እንደገለጹት፥ ዘላቂ ሰላምና ልማትን በማረጋገጥ የኢትዮጵያን የማንሰራራት ዘመን እውን ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ ነው። ለዚህም ሚኒስቴሩ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ላሉ ወጣቶች በበጎ ፍቃድ አገልግሎት ስልጠና በመስጠት ሀገራዊ መግባባትን ለማጠናከር እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ወጣቶች የኢትዮጵያውያንን የአብሮነት እሴት በማጎልበት ለሕብረተሰቡ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት የሚሰጡበትንና የእርስ በእርስ ግንኙነትን የሚያጠናክሩበትን አቅም ለመፍጠር እየሰራ መሆኑንም አቶ አበበ ተናግረዋል። ወሎ ዩኒቨርሲቲን ጨምሮ በአምስት ዩኒቨርሲቲዎች ስልጠናው እየተሰጠ መሆኑንና ለአንድ ወር እንደሚቆይ ገልጸው፥ በስልጠናው ከ6 ሺህ በላይ ወጣቶች ይሳተፋሉ ብለዋል። እንደ አማካሪው ገለጻ ስልጠናው በሀገር ፍቅር፣በሰብዕና ግንባታ፣ በስነ ምግባር፣ በብሔራዊ መግባባትና በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ወጣቶች ተጨማሪ እውቀት እንዲጨብጡ የሚያደርግ ነው። ባለፉት ለ13 ዙር በተሰጡ ስልጠናዎች ከ100 ሺህ በላይ በጎ ፍቃድ ወጣቶች ስልጠና ወስደው ሕብረተሰቡን በበጎ ፍቃድ ከማገልገል ባለፈ ለተለያየ ኃላፊነት የበቁበት ሁኔታ እንዳለም አመልክተዋል። የወሎ የኒቨርሲቲ አስተዳደርና ልማት ምክትል ፕሬዚዳንት ተወካይ አቶ ጌትነት ካሴ በበኩላቸው እንዳሉት፣ ዩኒቨርሲተው ሰላምን ለማጠናከርና ብሔራዊ መግባባት ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት በጥናትና ምርምር የበኩሉን እገዛ እያደረገ ነው። ከስልጠናው ተሳታፊዎች መካከል ወጣት ሳይመን ኮች በሰጠው አስተያየት፣ በየአካባቢው ያሉ የተለያዩ ባህሎች፣ ቋንቋና የተፈጥሮ ሀብቶችን አውቆ ሀገራዊ አንድነት ለመፍጠር በሚሰሩ ሥራዎች የድርሻውን ለመወጣት መዘጋጀቱን ገልጿል። የወጣቶችን ማህበራዊ ተሳትፎ ለማሳደግ በሚሰጠው ስልጠና ላይ መሳተፉ ይህን እውን ለማድረግ እንደሚያግዘውም ተናግረዋል። ስልጠናው ህብረ ብሔራዊነትንና አንድነትን በማጠናከር ለሀገር እድገት በጋራ እንድንሰራ መሰረት ይጥላል ያለችው ደግሞ ወጣት ረምላ መሀመድ ናት። በስልጠናው የምናገኘው እውቀት ሕብረተሰቡን በበጎ ፈቃድ እንድናገለግልና ሰላማችንን እንድናጸና ተጨማሪ አቅም ይሆናል ብላለች። በስልጠናው ማስጀመሪያ ላይ አመራሮች፣ የሃይማኖት አባቶችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።  
አገልግሎቱ ከነበረብን ችግር ወጥተን አዲስ ሕይወት እንድንጀምር ተስፋ ሰጥቶናል
Oct 12, 2025 58
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 2/2018 (ኢዜአ)፡-‎በኢትዮጵያ አካል ድጋፍ አገልግሎት ያገኙት ድጋፍ ከነበረባቸው ሱስ ተላቀው አዲስ የሕይወት ምዕራፍ እንዲጀምሩ ተስፋ እንደሆናቸው ቀደም ሲል በተለያየ ሱስ ተጠምደው የነበሩ ግለሰቦች ገለጹ። ኢዜአ ያነጋገራቸው በተለያየ ሱስ ተጠምደው የነበሩ ግለሰቦች የቤተሰብ መበታተን፣ የሥራ ማጣት እና የከፍተኛ የጤና መቃወስ አደጋ እንዳስከተለባቸው ይናገራሉ። ነገር ግን፣ በኢትዮጵያ አካል ድጋፍ አገልግሎት ያገኙት ድጋፍ ለብዙዎች ከጨለማው ጉዞ ወጥተው አዲስ የሕይወት ምዕራፍ እንዲጀምሩ እንዳስቻላቸው ይገልፃሉ፡፡ ‎ወጣት እንዳለልኝ ታዬ ለዓመታት በመጠጥና በጫት ሱስ ሲሰቃይ እንደነበር ይናገራል። ሱሱ በሕይወቱ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንዳደረሰበትና ወደ ውድቀት እንዳመራው በቁጭት ይገልጻል፡፡ ከዚህ አስከፊ ሕይወት ለመውጣት መወሰኑን ተከትሎ ወደ አገልግሎቱ መግባቱን ከሱስ ነጻ መሆን መቻሉን በደስታ ይናገራል። ‎በተመሳሳይ፣ ጌትነት ተረፈ በአገልግሎቱ ውስጥ ባሳለፋቸው ጊዚያት ከሱስ ነጻ የሚያደርገውን አገልግሎት እና እንክብካቤ ማግኘቱን ይገልጻል፡። ጌትነት የሥነ ልቦና ድጋፍን ጨምሮ የተለያዩ አስፈላጊ አገልግሎቶች እንደተሰጠው ጠቅሶ፣ በተደረገለት በቂ ድጋፍና እንክብካቤ ምክንያት ከሱስ ነጻ መሆኑን አመላክቷል። ‎አዲስ ሕይወት የጀመሩት እነዚህ ተጠቃሚዎች ለቀጣይ ሕይወታቸውን ለመቀየር ቁርጠኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። ቤተሰቦቻቸውን ለመርዳት፣ በትጋት ሠርተው ሕይወታቸውን ለመለወጥ እንደሚሠሩ ተናግረው፤ ወጣቶች ራሳቸውን ከሱስ እንዲጠብቁ አጥብቀው መክረዋል። ‎የኢትዮጵያ አካል ድጋፍ አገልግሎት ሜዲካል ዳይሬክተር ዶክተር ገረመው ወንዶ በበኩላቸው፤ አገልግሎቱ በተለያዩ ሱሶች የተጠመዱ ግለሰቦች ከነበረባቸው ችግር እንዲላቀቁ በትጋት እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። ወደ አገልግሎቱ ለሚመጡ ግለሰቦች ከሱስ እንዲያገግሙ ከሚረዳ ድጋፍ በተጨማሪ፣ ወደ ሥራ እንዲመለሱ የሚያስችላቸውን የክህሎት ሥልጠና ጭምር እንደሚሰጥ አብራርተዋል። በቀጣይ የሚሰጠውን አገልግሎት ለማሳደግ የማስፋፊያ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸው፤ በሱስ ችግር የተጠቁ ወደ ማዕከሉ በመምጣት አገልግሎት እንዲያገኙ ጥሪ አቅርበዋል።   ‎      
የወጣቱን የበጎ ፍቃድ አገልግሎትና የሰላም አምባሳደርነት ሚና የሚያሳደጉ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ--የሰላም ሚኒስቴር
Oct 12, 2025 73
ጅማ፣ ጥቅምት 2/2018(ኢዜአ)፡-የወጣቱን የበጎ ፍቃድ አገልግሎትና የሰላም አምባሳደርነት ሚና የሚያሳደጉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሰላም ሚኒስቴር አስታወቀ። በሰላም ሚኒስቴር አስተባባሪነት የሚተገበረው የ14ኛ ዙር የወጣቶች "የበጎነት ለአብሮነት" ስልጠና ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በጅማ ዩኒቨርሲቲ ተካሂዷል።   በስልጠናውም በቀጣይ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ብሔራዊ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት የሚሰጡ 1ሺህ ወጣቶች እንድሚሳተፉም ተመላክቷል። በሰላም ሚኒስቴር የብሔራዊ በጎ ፍቃድ ማህበረሰብ ልማት አገልግሎት ፕሮግራም መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ገመቺሳ ኢቲቻ በመርሀ ግብሩ ላይ እንዳሉት ወጣቱ በማህበራዊ በጎ ፍቃድ አገልግሎት መሪ እንዲሆን እየተሰራ ነው ። በተለይ ማህብረሰቡን በበጎ ፍቃድ አገልግሎት በማገዝ ማህበራዊ ሀላፊነቱን እንዲወጣ የማስተባበር ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቁመዋል። እንደ አቶ ገመቺስ ገለጻ ወጣቶች ለዘላቂ ሰላምና የህዝቦች አብሮነት ይበልጥ ተግተው እንዲሰሩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። ለተግባራዊነቱም ሰላም ሚኒስቴር ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመተባበር ወጣቶችን በ13 ዙር በማሰልጠን በተለያዩ አካባቢዎች ተንቀሳቅሰው ብሔራዊ በጎ ፍቃድ አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉን አስታውሰዋል። ይህም ሰላምን ከማጠናከር፣ በህዝቦች መካከል አብሮነትን ከማጎልበትና ብሔራዊ መግባባትን ከመገንባት አንጻር ጉልህ ሚና እንዳለው ነው የገለጹት። የወጣቱን የበጎ ፍቃድ አገልግሎትና የሰላም አምባሳደርነት ሚናን የሚያሳደጉ ተግባራት በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ ሲሉም አቶ ገመቺስ ተናግረዋል።   የጅማ ዩኒቨርሲቲ ቴክኖሎጂ ኢኒስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ኢንጂነር ኤፍሬም ዋቅጅራ በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በተለያዩ ዙሮች ለህብረተሰቡ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት የሚሰጡ ወጣቶችን ተቀብሎ ማሰልጠኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም ዩኒቨርሲቲው ከ1 ሺህ በላይ ወጣቶችን ተቀብሎ እንደሚያሰለጥን ገልጸው ዛሬ የተጀመረው ስልጠና ለአንድ ወር እንደሚቆይ ገልጸዋል።  
በበጎ ፍቃድ አገልግሎት በመሳተፍ የማህበረሰቡን ችግር ለማቃለል እየተሰራ ነው
Oct 12, 2025 75
አዳማ፤ጥቅምት 2/2018(.ኢዜአ)፦በበጎ ፍቃድ አገልግሎት በንቃት በመተሳተፍ የማህበረሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ማቃለል ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የገቢዎች ሚኒስትር አይናለም ንጉሴ ገለፁ። በኢትዮጵያ ጉሙሩክ ኮሚሽን አዳማ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት በአዳማ ከተማ ዳቤ ክፍለ ከተማ የተገነባው የከለቾ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ዛሬ ተመርቋል።   በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ የገቢዎች ሚኒስትር አይናለም ንጉሴ፣ የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ፣ የኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ የስራ ሃላፊዎች፣ አባ ገዳዎች፣ ሃደ ሲንቄዎችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል። የገቢዎች ሚኒስትር አይናለም ንጉሴ በወቅቱ እንደገለፁት፥ በበጎ ፍቃድ አገልግሎት በንቃት በመተሳተፍ የማህበረሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ማቃለል ላይ በትኩረት እየተሰራ ነው። "በአዳማ ከተማ በትምህርት ቤት ብቻ ሳይሆን የአቅመ ደካማ ቤቶችን ገንብተን አስረክበናል" ብለዋል። የትምህርት ቤቱ ግንባታ ዘመናዊ የመማሪያ ክፍሎችና የመምህራንና አስተዳደር ቢሮዎችን ያካተተ መሆኑን ተናግረዋል። ትምህርት ቤቱ በዕውቀትና ክህሎት የዳበረ ትውልድ ለመገንባት አስተዋጾው የጎላ መሆኑን አስታውቀዋል።   የኢትዮጵያ ጉሙሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ደበሌ ቃበታ በበኩላቸው፥ ኮሚሽኑ የሀገር ልማትና ዕድገት ለማስቀጠል የሚያግዘውን ገቢ ከማስገባት ባለፈ በበጎ ተግባር በስፋት እየተሳተፈ ይገኛል ብለዋል። የትምህርት መሰረተ ልማትን ጨምሮ ትላልቅ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ አስፈላጊውን ገቢ ከመሰብሰብ አኳያ የጀመርነውን ተግባር አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉም አክለዋል።   ኮሚሽኑ ከመደበኛ ስራው በተጓዳኝ በበጎ ፍቃድ አገልግሎት በመሳተፍ በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ አደጋ ለተጎዱ ወገኖች እንዲሁም የትምህርት ቁሳቁስ እጥረት ላጋጠማቸው ተማሪዎች በአይነትና በጥሬ ገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን አመልክተዋል። በአዳማ ከተማ ሶሎቄ ዶንጎሬ ወረዳ የተገነባው የከለቾ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤትም የዚሁ አካል መሆኑን አስታውቀዋል።   የኦሮሚያ ትምህርት ቢሮ ምክትል ሃላፊ ብልቶሳ ሂርኮ (ዶ/ር) እንደገለፁት፥ የክልሉ መንግስት በገጠርና በከተማ የትምህርት መሰረተ ልማት ተደራሽነትና ጥራት ማስጠበቅ ላይ በማተኮር እየሰራ ነው። በአዳማ የተገነባው ትምህርት ቤትም ይህንኑ ተግባር የሚያጠናክር መሆኑን አመልክተዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው፥ በከተማዋ የትምህርት ቤቶች ደረጃ ማሻሻያ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቁመው ፥ በኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን አዳማ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የተገነባው ትምህርት ቤትም አንዱ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰዋል።   የኮሚሽኑ የአዳማ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ መንግስቱ ባልቻ በበኩላቸው፥ ቅርንጫፉ በበጎ ፍቃድ አገልግሎት በመሳተፍ የተለያዩ ተግባራት ማከናወኑን ተናግረዋል። በአዳማ ዳቤ ክፍለ ከተማ ሶሎቄ ዶንጎሬ ወረዳ የከለቾ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ገንብተን በዛሬው ዕለት አስረክበናል ብለዋል።
በዞኑ በትምህርት ዘመኑ ለትምህርት ጥራት መጠበቅ ትኩረት ተሰጥቷል
Oct 12, 2025 54
ነቀምቴ፤ጥቅምት 2/2018(ኢዜአ)፦በምስራቅ ወለጋ ዞን በትምህርት ዘመኑ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ትኩረት መሰጠቱን የዞኑ ትምህርት ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ ትምህርት ጽህፈት ቤት ምክትል ሀላፊ አቶ ዘላለም አለሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ በዞኑ በትምህርት ዘመኑ ከ450 ሺህ በላይ ተማሪዎች ተመዝግበው ትምህርት ጀምረዋል።   በክረምት ወራት የትምህርት ተደራሽነትና ጥራትን ለማረጋገጥም የሚያግዙ 80 የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶች ለአገልግሎት መብቃታቸውን ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ አራት የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተገንብተው ለ2018 የትምህርት ዘመን አገልግሎት መጀመራቸውን ገልጸዋል። ከአዳዲስ የትምህርት ቤቶች ግንባታ ጎን ለጎን ነባር ትምህርት ቤቶችን የመጠገንና በትምህርት ቤቶች 460 ተጨማሪ የመማሪያ ክፍሎች የመገንባት ሥራ መከናወኑን አመልክተዋል። የመማር ማስተማር ሥራውን ምቹ ለማድረግም ግብአት ከማሟላት በተጨማሪ የትምህርት ምድረ ግቢ ውበት ሥራ መሰራቱን ተናግረዋል። ከዚህ ባለፈ 81 ሺህ ተማሪዎችን በትምህርት ቤት ምገባ መርሃ ግብር ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አመልክተዋል። በትምህርት ዘመኑ የተማሪዎችን ውጤት ለማሻሻል ከግብአት በተጨማሪ ለመምህራንን ልማት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ ሲሰራ መቆየቱንም አክለዋል። ጊዜውን በአግባቡ በመጠቀም ለተሻለ ውጤት እንደሚተጋ የገለጸው ደግሞ በዞኑ የቢፍቱ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ የአብስራ ታደሰ ነው። ሌላኛው ተማሪ ናኦል ደሳለኝ በበኩሉ፥ከመምህራን እገዛ በተጨማሪ ጊዜውን በቤተ መጻህፍት በማሳለፍ የተሻለ ውጤት ለማምጣት ከወዲሁ ተግቶ እየሰራ መሆኑን ተናግሯል።
በደሴ ከተማ በክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት የተገኘው ውጤት በበጋው ወራት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Oct 12, 2025 67
ደሴ፤ ጥቅምት 2/2018(ኢዜአ)፡- በደሴ ከተማ በክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት የተገኘው አበረታች ውጤት በበጋው ወራት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የከተማው አስተዳደር አስታወቀ። የከተማ አስተዳደሩ የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት ማጠቃለያና የበጋ ወቅት የአገልግሎቱ ማስጀመሪያ መድረክ ተካሂዷል።   በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የደሴ ከተማ ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰይድ የሱፍ እንደገለጹት፣ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት የሕብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር እየፈታ ነው። በክረምት ወቅት በተተገበረው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የአቅመ ደካሞችን ቤት መስራት፣ የተቸገሩ ቤተሰቦችን በመደገፍ፣ ማዕድ በማጋራት፣ ጎርፍ በመከላከል፣ በትምህርትና በጤናው ዘርፍ አበረታች ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። የተመዘገበውን ውጤትና የተፈጠረውን ከፍተኛ መነቃቃት በማጠናከር በበጋው ወራት ተግባሩ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። የከተማ አስተዳደሩ ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሰይድ አራጋው በበኩላቸው እንደገለጹት፣ በክረምቱ ከ133 ሺህ በላይ በጎ ፍቃደኞችን በማሳተፍ ከ128 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል።   በተግባሩም የ336 የአቅመ ደካማ ቤቶች አዲስ ግንባታና ጥገና፣ ችግኝ ተከላ፣ 2 ሺህ 990 የኒት ደም ልገሳና ሌሎችም አገልግሎቶች ተሰጥተዋል ብለዋል። በበጎ ፈቃድ ስራው በህዝብና በመንግስት ይወጣ የነበረውን በርካታ ገንዘብ ማዳን መቻሉን ጠቁመው የተገኘውን ልምድና ተሞክሮ በመጠቀም በበጋው ወራትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በበጋ በጎ ፍቃድ አገልግሎትም ከ39 ሺህ በላይ በጎ ፍቃደኞችን በማሳተፍ ከ40 ሺህ በላይ ሰዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ወደ ሥራ መገባቱን ገልጸዋል። በደሴ ከተማ በበጎ ፍቃድ አገልግሎት የተሳተፈችው ወጣት ሰናይት ምትኩ በሰጠችው አስተያየት፣ በክረምቱ የአቅመ ደካሞችን ቤት በመስራት፣ ደም በመለገስ፣ በከተማ ጽዳትና ውበት ተሳትፎ አድርጋለች።   በዚህም የሕብረተሰቡን ችግር ማቃለል መቻላቸውን ጠቁማ በበጋው በጎ ፍቃድ አገልግሎት በመሳተፍ ሕብረተሰቡን ለማገልገል መዘጋጀቷን ተናግራለች። ሕብረተሰቡን በበጎ ፍቃድ አገልግሎት በማገልገል የሕሊና እርካታ ማግኘቱን የገለጸው ደግሞ ወጣት ሰይድ አህመድ ነው።   ከሌሎች ጓደኞቼ ጋር በመሆን በአቅመ ደካሞች ቤት ግንባታ፣ በጎርፍ መከላከል፣ በደም ልገሳ፣ በማካካሻ ትምህርትና በሌሎችም በክረምት በጎ ፍቃድ ያሳየነውን ተሳትፎ በበጋው ወራትም አጠናክረን እንቀጥላለን ብሏል።   በመድረኩ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች፣ በጎ ፍቃደኞችና ሌሎችም የተገኙ ሲሆን የተሻለ አስተዋጽኦ ላበረከቱ በጎ ፍቃደኞች፣ ተቋማትና ግለሰቦች እውቅና ተሰጥቷል፡፡  
የአርሶ አደሩን ህይወት በመቀየር በኢትዮጵያ የሚታሰበውን ለውጥ ማምጣት ይቻላል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Oct 11, 2025 194
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 1/2018(ኢዜአ)፦ የአርሶ አደሩን ህይወት በመቀየር በኢትዮጵያ የሚታሰበውን ለውጥ እውን ማድረግ እንደሚቻል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከፌዴራል እና ከክልል አመራሮች ጋር የገጠር ኮሪደር ስራዎች ላይ ውይይት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የገጠር ኮሪደር ስራው ገጠርን የማሻገር እና የገጠሩን አርሶ አደር ህይወት የማዘመን አላማ ያነገበ መሆኑን ገልጸዋል። በሀላባ፣ ከምባታ፣ ሀዲያ እና ስልጤ ዞኖች የተሰሩት የሞዴል ገጠር መንደሮች ከፍተኛ ደስታን እንደሚፈጥሩም ተናግረዋል። የእያንዳንዱን አርሶ አደር ህይወት መቀየር ከተቻለ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እና በብዙ መልኩ የሚነሱ ችግሮችን ለመፍታት ያግዛል ብለዋል። በኢትዮጵያ ያለውን የመቀንጨር ችግር መቅረፍ የሚያስችሉ እንቁላል፣ ማር፣ ስጋ፣ ዶሮ፣ ፍራፍሬ፣ ጎመን እና ሰላጣን ጨምሮ በየጓሮው የሚለሙ በቂ ንጥረ ነገር ያላቸው ምግቦች እንዳሉ አንስተዋል። እነዚህን እየተመገበ ያደገ ሰው ሊቀነጭርና ሊራብ አይችልም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የገጠር ኮሪደር ስራ መቀንጨርን ለመከላከል እንደሚያግዝም አመልክተዋል። በዚህም የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ እና ምርቶችን ለገበያ በማቅረብ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ እንደሚቻል ነው ያነሱት። የገጠር ኮሪደር ስራን ለማስፋትና ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነት እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው፤ ይህን ኢኒሼቲቭ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ማስፋት ከተቻለ በኢትዮጵያ የሚፈለገውን ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል አመልክተዋል። የአርሶ አደሩን ኑሮ መቀየር መቻሉ አስደሳች መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህ መልካም ጅማሮ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም አሳስበዋል።
የ2017 ሀገራዊ የመጅሊስ ምርጫ በለውጡ መንግስት የተገኘ ታሪካዊ ስኬት ነው - ሸህ ሀጂ ኢብራሂም ቱፋ 
Oct 11, 2025 100
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 1/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የ2017 ሀገራዊ የመጅሊስ ምርጫ በለውጡ መንግስት የተገኘ ታሪካዊ ስኬት ነው ሲሉ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሸህ ሀጂ ኢብራሂም ቱፋ ገለፁ። የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የ2017 ሀገራዊ የመጅሊስ ምርጫ አስፈፃሚ ቦርድ የምርጫውን መጠናቀቅ ምክንያት በማድረግ የዕውቅናና ምሥጋና መርሐ ግብር አካሂዷል።   በመርሐ ግብሩ ቦርዱ ለምርጫው ስኬታማነት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላት እውቅናና ምስጋና ሰጥቷል። የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሸህ ሀጂ ኢብራሂም ቱፋ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ምርጫው በለውጡ መንግስት የተገኘ ታሪካዊ ስኬት ነው። የመጅሊሱ ምርጫ ጠንካራና ዘላቂ ኢስላማዊ ተቋም ለመፍጠር ያለመ እንደነበር ገልጸው፤ የተጠናቀቀው ሂደት የኢትዮጵያ ሙስሊሞችን አንድነት ያሳየ መሆኑን አብራርተዋል። ፕሬዝዳንቱ ምርጫው ሰላማዊና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ትልቅ ድርሻ ላበረከተው መንግስት ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን፤ ህዝበ ሙስሊሙ በምርጫው ላደረገው ተሳትፎም አመስግነዋል።   ፍትሃዊና ፍፁም ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ላበረከቱ ሁሉ ምስጋና ይገባል ሲሉም አክለዋል። የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የ2017 የመጅሊስ ምርጫ አስፈፃሚ ቦርድ ሰብሳቢ አብዱላዚዝ ኢብራሂም (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ከፌዴራል እስከ መስጂድ የተዋቀረው የምርጫ አስፈፃሚ ተቋማዊ ተልዕኮውን በስኬት አጠናቋል።   ምርጫው መላውን ህዝበ ሙስሊም ከጫፍ እስከ ጫፍ አሳትፎ በስኬት የተጠናቀቀ ሲሆን፤ በቀጣይ ለሚደረጉ ምርጫዎችም ትምህርት የተወሰደበት መሆኑን ገልጸዋል። በመጨረሻም የመጅሊሱ ምርጫ አስፈፃሚ ቦርድ አመራር አባላት በምርጫው ሂደት ውስጥ ለተሳተፉና ስኬታማ እንዲሆኑ ላደረጉ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።
በጤናው ዘርፍ የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት እየተደረጉ ባሉ ሁሉን አቀፍ ጥረቶች አበረታች ውጤት ተመዝግቧል
Oct 11, 2025 108
‎ባሕርዳር፤ ጥቅምት 1/2018(ኢዜአ)፡- በጤናው ዘርፍ የተቀመጡ የልማት ግቦችን ለማሳካት በክልሉ እየተደረጉ ባሉ ሁሉን አቀፍ ጥረቶች አበረታች ውጤት መመዝገቡን የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ገለጸ። ‎‎ቢሮው በክልሉ ከሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ጋር በጤናው ዘርፍ እያከናወኑት ባሉት ተግባራት ዙሪያ ዛሬ በባሕርዳር ከተማ የምክክር መድረክ አካሄዷል።   ‎‎የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ መልካሙ ጌትነት በመድረኩ ላይ እንዳመለከቱት፤ እንደሀገር በጤናው ዘርፍ የተቀመጡ የልማት ግቦችን ለማሳካት ክልሉ የድርሻውን እየተወጣ ነው ። በዚህም እየተደረጉ ባሉ ሁሉን አቀፍ ጥረቶች አበረታች ውጤት መመዝገቡን ገልጸው፤ በዚህም ተላላፊ በሽታዎች እየቀነሱ እና የእናቶችና ህፃናት ጤና እየተሻሻለ መምጣቱን ጠቅሰዋል። ‎የክልሉ የጤና ስርዓት እንዲሻሻልና በተላላፊ በሽታዎች መቀነስ ለተገኘው ውጤት በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን አንስተዋል። ‎በመሆኑም ጤናማና አምራች ዜጋን ለመፍጠር ቢሮው ከአጋር አካላት ጋር የጀመረውን ቅንጅታዊ አሰራር ይበልጥ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።ቢሮው የ25 ዓመት የጤናው ዘርፍ ፍኖተ ካርታ ማዘጋጀቱም ተመልክቷል። ‎የመድረኩ ተሳታፊ አጋር አካላት ለክልሉ የጤና ዘርፍ ውጤታማነት ሲያደርጉት የቆየውን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።   በምክክር መድረኩ ላይ የጤና ቢሮ አመራሮችና በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የሰቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ተሳትፈዋል።
በቴክኒክና ሙያ ዘርፍ የሰለጠኑ ወጣቶች  ከራሳቸው አልፈው ሀገራቸውን እየጠቀሙ ነው- ከንቲባ ከድር ጁሃር 
Oct 11, 2025 107
ድሬደዋ፤ ጥቅምት 1/2018(ኢዜአ)፦ በቴክኒክና ሙያ ዘርፍ በርካታ ወጣቶች እየሰለጠኑ እና ከራሳቸው አልፈው ሀገራቸውንም እየጠቀሙ መሆኑን የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ገለጹ። በድሬዳዋ የሚገኙት የድሬዳዋ ፖሊቴክኒክ እና የኢትዮ -ጣሊያን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጆች በተለያዩ የሙያ መስኮች ያሰለጠኗቸውን ወጣቶች አስመርቀዋል።   በዚሁ መርሃ ግብር ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር፤ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ከቴክኖሎጂ እና ዘመናዊ አሠራር ጋር በማስተሳሰር ለወጣቶች የአዳዲስ ስራ ፈጠራ አቅም መሆናቸውን ገልጸዋል። አዳዲስ የፈጠራ ስራዎችን በመስራት ከራሳቸው አልፈው በርካቶች ለሀገር ለውጥና የዕድገት እንቅስቃሴዎች የላቀ አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑንም አንስተዋል።   ለቴክኒክና ሙያ ዘርፍ በተሰጠው ትኩረት ወጣቶች እየሰለጠኑና እየሰሩ ከራሳቸው አልፈው ሀገራቸውን እየጠቀሙ ይገኛሉ ብለዋል። በመሆኑም ተመራቂዎች በሰለጠኑበት ሙያ ፈጠራቸውንና ብቃታቸውን በመጠቀም ለለውጥ እንዲተጉ ከንቲባው መልእክታቸውን አስተላልፈዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር የስራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ሮቤል ጌታቸው፤ በአስተዳደሩ ክህሎት መር የስራ ዕድል ፈጠራን በላቀ ጥራት ለማሳካት እየተሰራ መሆኑን ገልጸው ወጣቶች በቀሰሙት ዕውቀት ለራሳቸውና ለከተማቸው ለውጥ እንዲሰሩ አስገንዝበዋል።   በድሬዳዋ፤ የድሬዳዋ ፖሊቴክኒክ እና የኢትዮ -ጣሊያን ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጆች ከደረጃ አንድ እስከ አምስት ያሰለጠኗቸውን 1 ሺህ 42 ወጣቶችን ነው ያስመረቁት።
በድሬዳዋ አስተዳደር የተሻለ ውጤት ላስመዘገቡ ተማሪዎች እውቅና እና ሽልማት ተሰጠ 
Oct 11, 2025 83
ድሬደዋ፤ ጥቅምት 1/2018(ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ አስተዳደር በ2017 ዓ.ም የተሻለ ውጤት ላስመዘገቡ ተማሪዎች እውቅና እና ሽልማት ተሰጠ። በእውቅናና ሽልማት መርሃ ግብሩ ላይ የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር፤ የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሱልጣን አልይ እና ሌሎች የአስተዳደሩ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዚህም በ2017 ዓ.ም የ12ተኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተናን 574 በማምጣት ከፍተኛውን ውጤት ያስመዘገበችው ተማሪ አፎሚያ ጋሹ ከ250 ሺህ ብር በላይ የሚያወጡ የኤሌክትሮኒክስ ቁሶችና 45 ሺህ ብር ሽልማት ተበርክቶለታል።   የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር በወቅቱ እንደተናገሩት፤ አምና ለተመዘገበው የተሻለ ውጤት የመምህራንና የወላጆች የተቀናጀ ድጋፍና ክትትል እንዲሁም በትምህርት ዘርፍ የተሰሩ የለውጥ ስራዎች ማሳያ ናቸው። አስተዳደሩ ለትምህርት ጥራትና ተደራሽነት በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው ወላጆች ከመምህራንና ትምህርት ቤቶች ጋር የጀመሩትን የድጋፍና የክትትል ስራዎች በማጠናከር የተሻለ ውጤት እንዲመጣ መትጋት እንዳለባቸውም አሳስበዋል።   ተሸላሚዎች በቀጣይም ትምህርታቸውን በትጋት በመከታተልና ውጤታማ በመሆን ሃገርን ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ መስራት እንዳለባቸው አስታውሰዋል። ከተሸላሚዎቹ መካከል የተማሪ አፎሚያ አባት አቶ ጋሹ ሙሉ እንዳሉት፤ ተማሪዎች የተሻለ ውጤት እንዲያመጡ የወላጅ ድጋፍና ክትትል መሰረታዊ ጉዳይ ነው ። "እኛ በቤት ውስጥ ከምናደርገው ድጋፍ ባሻገር ከትምህርት ቤቶች ጋር በመቀናጀት ያደረግነው ክትትል ጥሩ የሚባል ነው'' ሲሉ ተናግረዋል። በ12ኛ ክፍል አገር አቀፍ ፈተና 543 በማስመዝገብ ተሸላሚ የሆነው ተማሪ አቡበከር ካሊድ እና በማህበራዊ ሳይንስ 500 በማምጣት የተሸለመችው ተማሪ ኤፍራታ ኢሳያስ፣ ሽልማቱ ወደ ፊት የበለጠ ትምህርታቸውን በርትተው እንዲማሩ እና ተተኪዎች እንዲነቃቁ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል።   የድሬዳዋ አስተዳደር በዘንድሮ አመት የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ በተቀናጀ መንገድ እየሰራ መሆኑን የገለፁት ደግሞ አስተዳደሩ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሱልጣን አልይ ናቸው።  
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወባ በሽታን ለመከላከል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው
Oct 11, 2025 78
ወላይታ ሶዶ፤ ጥቅምት 1/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወባ በሽታን ለመከላከልና የህብረተሰቡን ጤንነት ለመጠበቅ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ እንዳሻው ሽብሩ፤ በክልሉ የወባ መከላከልና የህክምና አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግ ረገድ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በማብራሪያቸውም በክልሉ ለወባ ተጋላጭ የሆኑ አካባቢዎችን በመለየት በተቀናጀ መልኩ የመከላከል፣ የቁጥጥር፣ ክትትልና ድጋፍ እንዲሁም የህክምና አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። ለወባ መራቢያ ምቹ የሆኑ ስፍራዎችን በማጽዳትና ማህበረሰቡም የመከላከያ መንገዶችን እንዲከተል እየተደረገ መሆኑን አንስተው ፤ አሁን ላይ 91 ሺህ ከረጢት ኬሚካል እና 556 ሺህ የአልጋ አጎበሮች ስርጭት መደረጉንም ጠቅሰዋል። የወባ መከላከሉ ስራ በቅንጅት በመሰራቱ የስርጭት መጠኑ እየቀነሰ ቢሆንም በቀጣይ ብዙ ስራ የሚጠይቅ ስለመሆኑ ተናግረዋል። የወላይታ ሶዶ ከተማ ጤና መምሪያ የበሽታ መከላከል ዘርፍ ኃላፊ በረከት ብርሃኑ፤ የወባ ስርጭትን ለመከላከል ከህዝቡና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   በወላይታ ሶዶ እና አካባቢው ነዋሪዎችም በባለሙያዎች ምክር፣ አጎበር በመጠቀምና አካባቢዎችን በማጽዳት ጭምር ወባን እየተከላከሉ መሆኑን ተናግረዋል።
የዳበረ የሲቪል ምዝገባ ስርዓት የጤናና ትምህርት አገልግሎቶችን በማረጋገጥ ዘላቂ የልማት ግቦችን ማሳካት ያስችላል 
Oct 11, 2025 68
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 1/2018 (ኢዜአ)፡-የዳበረና የተደራጀ የሲቪል ምዝገባ ስርዓት የጤናና ትምህርት አገልግሎቶችን በማረጋገጥ የ2030 ዘላቂ ልማት ግቦችን ማሳካት እንደሚያስችል የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሰሀረላ አብዱላሂ ገለጹ። ስምንተኛው የሲቪል ምዝገባና ቫይታል ስታቲስቲክስ ቀን "የሲቪል ምዝገባ ለህብረተሰቡ የዲጂታል መሰረተ ልማትና ህጋዊ ማንነት ስርዓት መሰረት ነው" በሚል መሪ ሀሳብ እየተከበረ ነው። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሰሀረላ አብዱላሂ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ የዳበረና በአግባቡ የተደራጀ የሲቪል ምዝገባ ስርዓት ልደትና ሞትን ጨምሮ የወሳኝ ኩነቶችን ምዝገባ ያረጋግጣል። ለዚህም ዜጎች ለምዝገባ ማረጋገጫ አስፈላጊ የሆኑ የምስክር ወረቀት እንዲያገኙ ይደረጋል ብለዋል።   ከሲቪልና ቤተሰብ ምዝገባ ስርዓት የሚገኝ መረጃ ለአንድ ሀገር ልማት፣ ለፖሊሲና ስትራቴጂ ቀረፃ እንዲሁም ለተሟላ የዕቅድ ዝግጅት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። የ2030 ዘላቂ የልማት ግቦችን ዕውን ለማድረግ የተጀመረው ጥረት የበለጠ ትክክለኛ እንዲሆን ያደርጋል ብለዋል። የወሳኝ ኩነት ምዝገባና ቫይታል ስታቲስቲክስ ስርዓት የአንድ ግለሰብ ከመንግሥት ጋር ለሚኖረው ግንኙነት የሰነድ ማስረጃ ሆኖ የሚያገለግል መሆኑን ገልጸዋል። እንደ ጤናና ትምህርት ያሉ መሰረታዊና አስፈላጊ አገልግሎቶችን ለማግኘትና የንብረት ባለቤትነትን ለማረጋገጥ ያስችላል ብለዋል። ከ17ቱ ዘላቂ የልማት ግቦች 12ቱ፤ ከ232 የዘላቂ ልማት ግቦች አመላካቾች መካከል 67 በወሳኝ ኩነቶች መረጃ ላይ የተመረኮዙ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ መረጃው የእናቶችና ጨቅላ ህፃናትን ሞት ለመቀነስና ድህነትን ለማስወገድ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። ስለሆነም አካታችና ቀጣይነት ያለው ሆኖ ምዝገባው በህግ ተደግፎ ተግባራዊ መሆኑን ገልጸዋል። በአዋጁ በጤና ተቋምና ከጤና ተቋም ውጭ የሚከሰቱ የልደትና የሞት ኩነቶችና የሞት ምክንያት የሚያሳውቁ የጤና ባለሙያዎች በመላ ሀገሪቷ እንዲሰማሩ መደረጉን ገልጸዋል። በዚህም የልደትና የሞት ኩነትና የሞት ምክንያት ማሳወቂያ መስጠት ከተጀመረበት 2010 ዓ.ም አጋማሽ ወዲህ በየዓመቱ እድገት በማሳየት በ2017 በጀት ዓመት መጨረሻ በሀገራችን በህይወት ከተወለዱ ህፃናት መካከል 82 በመቶ ማሳወቂያ መሰጠቱን ገልጸው፤ ከሞት አኳያ የተሰጠው ማሳወቂያ ከአምስት በመቶ በታች መሆኑን ተናግረዋል። እነዚህን ክፍተቶች በማረም የተሻለ የሲቪል ምዝገባ ስርዓት ለማከናወን ሁላችንም በትብብርና በትኩረት መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም