ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
በ "ቡሳ ጎኖፋ" የመረዳዳት ባህል ሕዝቡ ከ16 ሺህ በላይ የቁም እንስሳትን በማሰባሰብ በድርቅ ለተጎዱ 8 ሺህ አባ ወራዎች ድጋፍ አድርጓል - ቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ
Jun 3, 2023 16
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ) ፦ በ "ቡሳ ጎኖፋ" የመረዳዳት ባህል ሕዝቡ ከ16 ሺህ በላይ የቁም እንስሳትን በማሰባሰብ በድርቅ ለተጎዱ 8 ሺህ አባ ወራዎች ድጋፍ ማድረጉን ቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ አስታወቀ። ድጋፉ ሕብረተሰቡ የተለያዩ የቁም እንስሳቶችን በባህሉ መሰረት በማሰብሰብ በድርቅ ተጎጂ የሆኑ አባ ወራዎች ከጉዳታቸው አገግመው ራሳቸውን እንዲችሉ ያደረገው በጎ ተግባር መሆኑም ተገልጿል፡፡ የቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ ምክትል ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ማሊቻ ሎጄ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ 10 ዞኖች ተፈጥሮ የነበረው ድርቅ በሕዝቡ እና በእንስሳት ላይ ጉዳት አድርሷል፡፡ በመንግስት በኩል ድርቁን ለመቋቋም በተሰራው ስራ በድርቁ ሳቢያ ለተጎዱ 3 ነጥብ 9 ሚሊዮን ዜጎች ከ2 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የምግብ እህል ድጋፍ መደረጉን አመልክተዋል። በሌላ በኩል የተለያዩ አካላት ድጋፍ ያደረጉት ከ180 ሺህ በላይ ኩንታል የምግብ እህል ለተጎጂዎች መሰራጨቱን ተናግረዋል። አሁን ላይ በድርቅ ተጎጂ በነበሩ አካባቢዎች ላይ ዝናብ በመጣል ላይ መሆኑን ገልጸው፤ ተጎጂዎች ራሳቸውን እስኪችሉ ድረስ ድጋፍ ይደረጋል ነው ያሉት ዶክተር ማሊቻ። ቡሳ ጎኖፋ የኦሮሞ ሕዝብ ከጥንት ጀምሮ ሰው ሰራሽም ይሁን ተፈጥሯዊ አደጋዎች ሲያጋጥሙት እርስ በርስ የሚረዳዳበት ስርዓት መሆኑን ገልጸዋል። በዚህ ባህል መሰረት ባለፉት ጊዜያት ሕብረተሰቡ ከ100 ሺህ ኩንታል በላይ እህል በማሰባሰብ ለቦረና፣ ባሌ፣ ጉጂ እና ሐረርጌ ዞኖች ለድርቅ ተጎጂዎች ማድረሳቸውን አስታውሰዋል። በተጨማሪም ከ16 ሺህ በላይ የቁም እንስሳትን በማሰባሰብ ከ8 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የድርቅ ተጎጂ አባ ወራዎች ድጋፍ ማድረጉን በመጥቀስ። መንግስት ድርቅ በተከሰተባቸው አከባቢዎች ዘላቂ የሆኑ የልማት ፕሮጀክቶችን በማከናወን ላይ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ ለዚህም በርካታ ግድቦች ተገንብተው የዝናብ ውሃ መያዛቸውን ገልጸዋል። በሌላ መልኩ ዝናብ መዝነቡን ተከትሎ አርሶ አደሩና ከፊል አርብቶ አደሩ ወደ ሰብል ልማት እንዲገባ በመንግስት በኩል የዘር፣ የትራክተር እና የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት ተደራሽ መደረጉን ተናግረዋል። አርሶ አደሩም በሰብል ልማት ስራው ላይ ትኩረት በማድረግ በምግብ ዋስትና ራሱን ለመቻል በትኩረት እንዲሰራ ድጋፉ ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት። በቦረና ዞን ከ5 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ 18 የውሃ ግድቦች ግንባታ የተከናወነ ሲሆን በአካባቢው በዘነበው ዝናብም 12 ግድቦች ውሃ መያዛቸው ተጠቁሟል። ”ቡሳ ጎኖፋ” የገዳ ስርዓት አካልና የኦሮሞ ሕዝብ ጥንታዊ የመረዳጃ ስርዓት ሲሆን፤ የኦሮሞ ህዝብ ሰው ሰራሽም ይሁን ተፈጥሯዊ ችግር ሲያጋጥመው ችግሩን ለማለፍ እርስ በርስ የሚረዳዳበት ባህላዊ እሴት ነው።
በመዲናዋ የጎርፍ አደጋን ለመከላከል የፍሳሽ ማስተላለፊያ መስመሮች በደረቅ ቆሻሻ እንዳይዘጉ ሕብረተሰቡ በባለቤትነት መጠበቅ እንደሚገባው ተገለጸ
Jun 3, 2023 23
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ)፡- በአዲስ አበባ በመጪው ክረምት የጎርፍ አደጋን ለመከላከል የፍሳሽ ማስተላለፊያ መስመሮች በቆሻሻ እንዳይዘጉ ሕብረተሰቡ በባለቤትነት እንዲጠብቅ የከተማው ጽዳት አስተዳደር ኤጀንሲ ጥሪ አቀረበ። በአዲስ አበባ አራዳ ክፍለ ከተማ ወረዳ ሰባት ሳንፎርድ ኢንተርናሽናል ትምህርት ቤት አካባቢ የፍሳሽ ማስተላለፊያ መስመሮችን የማጽዳት ከተማ አቀፍ የፅዳት ንቅናቄ መርሐ-ግብር ዛሬ ተካሄዷል። "የከተማችን የፍሳሽ ማስተላለፊያ መስመሮች የውሃ መውረጃ እንጂ የቆሻሻ መጣያ አይደሉም!" በሚል መሪ ቃል የተጀመረው መርሃ ግብር ለቀጣይ ሶስት ወራት እንደሚቆይ ተገልጿል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ታረቀኝ ወርቅነህ፤ አካባቢን ማፅዳት ብቻ ሳይሆን ዳግም የቆሻሻ መጣያ ቦታ እንዳይሆኑ ነዋሪው በባለቤትነት መጠበቅ እንዳለበት ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ፅዳት በመጠበቅ ረገድ ማህበረሰቡ የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ ጠይቀዋል። የአዲስ አበባ ጽዳት አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር እሸቱ ለማ፤ በውሃ ማፍሰሻ ቱቦዎች በሕገወጥ መንገድ የሚጣሉ ቆሻሻዎች የጎርፍ አደጋ እንዲከሰት እያደረጉ ነው ብለዋል። ሕብረተሰቡ በዚህ የፅዳት ንቅናቄ በሁሉም የመዲናዋ አካባቢዎች የሚገኙ የፍሳሽ ማስወገጃ መስመሮችን በባለቤትነት በማፅዳት በመጪው ክረምት ሊፈጠር የሚችል የጎርፍ አደጋን በመከላከል ረገድ የበኩሉን መወጣት እንደሚገባ ገልጸዋል። ቆሻሻን በግዴለሽነት በየቦታው የሚጥሉ ግለሰቦችንና ድርጅቶችን ተጠያቂ ለማድረግ የአሰራር ደንብ መሻሻሉንም ነው ዶክተር እሸቱ ያመለከቱት። የአራዳ ክፍለ ከተማ የጽዳት አስተዳደር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ለምለም ንጉሴ በክፍለ ከተማው ካለፈው ሳምንት ጀምሮ እየተካሄደ ባለው የውሃ መውረጃ ቱቦዎችን ከደረቅ ቆሻሻ የማጽዳት ንቅናቄ 15 ሺህ ነዋሪዎች ተሳታፊ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በጽዳት መርሐ ግብሩ በየሳምንቱ በቋሚነት በጎ ፈቃደኞች እና የብሎክ ነዋሪዎች እየተሳተፉ መሆኑንም አመልክተዋል።
የቀቤና ብሄረሰብ የባህል ማዕከል ተመረቀ
Jun 3, 2023 30
ወልቂጤ ግንቦት 26 /2015 (ኢዜአ)፦ በቀቤና ልማት ማህበር በወልቂጤ ከተማ የተገነባው የቀቤና ባህል ማዕከል በደማቅ ሥነ ስርዓት ተመረቀ። በስነ-ስርዓቱ ላይ የደቡብ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋጤ ስርሞሎን ጨምሮ የፌደራልና የክልል ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል። በተጨማሪም የደቡብ ክልል የተለያዩ ብሔረሰቦች፣ የኦሮሚያ፣ የሲዳማ እና የሐረሪ ክልሎች እንዲሁም የአገር ሽማግሌዎች ተገኝተዋል። የቀቤና ልማት ማህበር የቦርድ ሰብሳቢ አቶ ከማል ሱልጣን እንደገለጹት፤ የባህል ማዕከሉ የብሔረሰቡን ባህል፣ ታሪክና ቋንቋ ጠብቆ ለማቆየት ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል። ማዕከሉ ሙዚየም፣ ቤተ መጽሐፍት እና የመሰብሰቢያ አዳራሾች እንዳሉት ገልፀው፤ ትውልዱ ነባር እሴቶችን እንዲያውቅ የሚያስችል ቅርሶችን የያዘ መሆኑን አመልክተዋል። የልማት ማህበሩ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራትን ከመንግስት ጋር ተቀራርቦ እየሰራ እንደሆነ ጠቅሰው፤ በቀጣይ የተለያዩ የልማት ስራዎችን ለመስራት የሚያስችል ስትራቴጂካዊ ዕቅድ መንደፉን ጠቁመዋል።
የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ጥበቃና ድጋፍ ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ የምክክር መድረክ እየተካሄደ ነው
Jun 3, 2023 31
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ) የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ጥበቃና ድጋፍ ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ ግብዓት ማሰባሰብ ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በአዳማ ከተማ እየተካሄደ ነው። የምክክር መድረኩ በሰላም ሚኒስቴር፣ በፍትሕ ሚኒስቴር፣ በዓለም አቀፉ ፍልሰተኞች ድርጅት እና በተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ኤጀንሲ ትብብር ተዘጋጅቷል። በመድረኩ የሰብዓዊ መብት ተቋማት፣ የሲቪል ማህበራት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ተወካዮችና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል። የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ስዩም መስፍን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ባለፉት ዓመታት በሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋ እናቶችና ህፃናትን ጨምሮ በርካታ ዜጎች ተፈናቅለዋል። በኢትዮጵያ እስካሁን ለሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች የተሟላ ድጋፍ ማድረግ የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ እንዳልነበረ አንስተዋል። በዝግጅት ሂደት ላይ የሚገኘው የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ጥበቃና ድጋፍ ረቂቅ አዋጅም ሰብዓዊ እርዳታ፣ የመብት ጥበቃን ጨምሮ ሌሎችም ድጋፎች እንዲደረጉላቸው እንደሚረዳ ጠቅሰዋል። በዓለም አቀፍ ተሞክሮ መንግስታት ተፈናቃዮችን በተሟላ መልኩ ለመርዳት የአቅም ውስንነት ስለሚያጋጥማቸው የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ተራድኦ ድርጅቶችን እንደሚያሳትፉ ተናግረዋል። በሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋ ምክንያት የሚከሰት የሀገር ውስጥ መፈናቀል በዜጎች ላይ የሚያሳርፈውን ዘርፈ ብዙ ጫና ለመቅረፍ ቅንጅታዊ የአሰራር ስርዓትን በህጋዊ አግባብ ለመምራትም ረቂቅ አዋጅ እየተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል። በረቂቅ አዋጁ መሰረት ተጠሪነቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የሆነ ብሔራዊ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ጥበቃና ድጋፍ ምክር ቤት እንደሚቋቋም ተጠቁሟል። ምክር ቤቱ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራ ሆኖ የተለያዩ የመንግስት ተቋማትን፣ የኃይማኖት ተቋማትን፣ የክልል ርዕሳነ መስተዳድሮችን እና እንደ አግባብነቱ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲካተቱ የሚደረጉ ሌሎች የሚመለከታቸው አካላትን ያቀፈ እንደሚሆን ተጠቁሟል።
የሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ለመታገል የጀመርነውን ጥረት እናጠናክራለን- በደቡብ ክልል የዘርፉ ባለሙያዎች
Jun 3, 2023 31
ሀዋሳ ግንቦት 26 /2015 (ኢዜአ)፡- በተቋማት ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ለመታገል የጀመሩትን ጥረት አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በደቡብ ክልል በተለያዩ ተቋማት የተመደቡ የጸረ ሙስና ክፍል ዳይሬክተሮችና ቡድን መሪዎች ገለጹ። የክልሉ ስነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን በበኩሉ፤በየተቋማቱ ያሉ የጸረ ሙስናና ስነምግባር መከታተያ ክፍሎችን በአዲስ መልክ ለማደራጀት እየተሰራ መሆኑን ገልጿል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የተቋማት ዳይሬክተሮችና ቡድን መሪዎች፤ በተመደቡበት ተቋም የአሰራር ግድፈቶችን ለማስተካከል ከክልሉ ስነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን ጋር በቅንጅት እንደሚሰሩ ተናግረዋል። በየተቋማቱ የሚታዩ ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን በመታገልም እንደሃገር እየተከናወነ ላለው የጸረ ሙስና ትግል ንቅናቄ ውጤታማነት የድርሻቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል። የሃላባ ዞን ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን መምሪያ የስነ ምግባርና ጸረሙና ቡድን መሪ አቶ ተመስገን ሱዱኖ እንዳሉት፤ የሚሰሩበት ተቋም ለሙስና ተጋላጭ ከሆኑት ውስጥ ይጠቀሳል። በተለይም ከመሬትና ገቢ አሰባሰብ ጋር ተያይዞ የሚታዩ ብልሹ አሰራሮች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ ችግሩን የፈጠሩ ባለሙያዎችን ከቦታው ማንሳትን ጨምሮ የተለያዩ አስተዳደራዊ እርምጃ እንዲወስድ የሚጠበቅባቸውን መወጣታቸውን ተናግረዋል። የደቡብ ክልል አርብቶ አደር ጉዳዮች ቢሮ የስነ ምግባርና ጸረ ሙስና ዳይሬክተር ወይዘሮ አበራሽ ኢሊጎ፤ መስኖን ጨምሮ በተለያዩ የአርብቶ አደር አካባቢዎች የልማት ፕሮጀክቶች የሚከናወንበት ተቋም መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም ከዲዛይንና ግንባታ ጋር ተያይዞ ሊፈጠሩ የሚችሉ ክፍተቶችን በመከታተል ለሙስናና ብልሹ አሰራር ተጋላጭ እንዳይሆን በትኩረት እየሰራን ነው ብለዋል። አርብቶ አደር አካባቢ በርካታ የልማት ጥያቄ መኖሩን ያነሱት ዳይሬክተሯ ፤ ለፕሮጀክት የተመደበው ገንዘብ በአግባቡ ስራ ላይ መዋሉን በመከታተል የህዝቡ ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ ሃላፊነታቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል። ለሙስና ተጋላጭ በሆኑ ተቋማት አሰራሩን በየጊዜው መፈተሽና ለውጤታማነቱ የባለሙያዎችን አቅም ማጎልበትና ከለላ መስጠት እንደሚያስፈልግም ጠቁመዋል። በመንግስት ተቋማት ውስጥ የስነ ምግባርና ጸረ ሙስና መከታተያ ክፍሎች መኖራቸው የሙስና ተጋላጭነታቸውን ይቀንሳል ያሉት ደግሞ የጋሞ ዞን ኢንቨስትመንት መምሪያ ስነ ምግባርና ጸረ ሙስና ቡድን መሪ አቶ ስንታየሁ ንጉሴ ናቸው። በጸረ ሙስና ትግሉ ተገቢውን ለውጥ ማምጣት እንዲቻል የባለሙያዎችን አቅም ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል። በተቋማት የተመደቡ ባለሙያዎችም ስለሚሰሩበት ተቋም ተገቢው እውቀት ኖሯቸውና ከሃላፊዎች ጋር በቅርበት ሰርተው እንደ ክልልም ሆነ እንደ ሃገር የተጣላባቸውን ሃላፊነት መወጣት አለባቸው ብለዋል። የተመደቡበት ተቋም ከኢንቨስትመንት ጋር ተያይዞ ለሙስናና ብልሹ አሰራር ተጋላጭ የሚሆንበት እድል በመኖሩ ስራዎችን በቅርበት የመከታተል ሃላፊነታቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል። የደቡብ ክልል ስነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ አማኑኤል አብደላ በበኩላቸው፤ በክልሉ እየተከናወነ ባለው የጸረ ሙስና ትግል የተቋማት ስነ ምግባርና ጸረ ሙስና ዳይሬክተሮችና ቡድን መሪዎች ሚና ከፍተኛ ነው ብለዋል። በዚህም ባለፉት ዘጠኝ ወራት በባለሙያዎች ክትትል በተከናወነው የቅድመ መከላከል ሥራ ከ293 ሚሊዮን ብር በላይ ሊመዘበር የነበረና የተመዘበረ ገንዘብ ብር ማዳን መቻሉን ጠቁመዋል። ይህንን ውጤታማ ተግባር ለማጠናከር በየተቋማቱ ያሉ የጸረ ሙስናና ስነምግባር መከታተያ ክፍሎችን በአዲስ መልክ የማደራጀት ተግባር አቅጣጫ ተቀምጦ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም በባለሙያ ደረጃ የነበረውን አደረጃጀት በክልል በዳይሬክተር፤ በዞንና ወረዳ ደግሞ በቡድን መሪዎች እንዲመራ መደረጉን ጠቅሰዋል ። ተገቢ መረጃ ይዘው ሙስናና ብልሹ አሰራርን መከላከል እንዲችሉ በየተመደቡበትም ተቋም የፊት አመራረነት ተሳትፎ እንዲኖራቸው መደረጉን ተናግረዋል። እንደ ሀገር አሳሰቢ ደረጃ ላይ የደረሰውን የሙስናና ብልሹ አሰራሮች ለመከላከልና ለመቆጣጠር ግብረ ሀይል ተደራጅቶ በልዩ ትኩረት እየተሰራበት መሆኑ ተመልክቷል።
የክልል የፀረ-ሙስና ኮሚቴዎች የሙስና ወንጀል በፈጸሙ የመንግሥት አመራሮችና ሌሎች በርካታ ግለሰቦች ላይ ህጋዊ እርምጃ መወሰዱን ገለጹ
Jun 3, 2023 44
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ)፡- በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን የፀረ-ሙስና ትግል ለማጠናከር በየክልሉ የተሰየሙ የፀረ-ሙስና ኮሚቴዎች የሙስና ወንጀል በፈጸሙ የመንግሥት አመራሮችና ሌሎች በርካታ ግለሰቦች ላይ ህጋዊ እርምጃ መወሰዱን ገለጹ። ኮሚቴዎች የምርመራና የተጠያቂነት ስራን በተጠናከረ መልኩ እያስቀጠሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል። የሙስና ወንጀል በኢትዮጵያ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ተከትሎ መንግስት ሰባት አባላት ያሉት የጸረ- ሙስና ብሔራዊ ኮሚቴ በህዳር ወር 2015 ዓ.ም ማቋቋሙ ይታወቃል። ይህንን ተከትሎ ክልሎችና ከተማ መስተዳደሮችም አምስት አባላት ያሉት ኮሚቴን በማቋቋም ሙስናን የመከላከልና ተጠያቂነትን የማስፈን ስራ እያከናወኑ መሆኑም እንዲሁ። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ የሲዳማ፣ የሃረሪና የጋምቤላ ክልል የስነ-ምግባርና ጸረ-ሙሰና ኮሚሽኖች ኮሚቴው የሙስና ትግሉ እንዲፋጠን በማድረግ ረገድ የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም ተጠያቂነትን በማረጋገጥና ፍትህን በማስፈን ረገድ ኮሚቴው የተቋቋመበትን ዓላማ በቁርጠኝነት እየተወጣ ስለመሆኑም ጠቁመዋል። የሲዳማ ክልል የስነ-ምግባርና ጸረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘላለም ለማ፤ በክልሉ ሙስናን ለመከላከል፣ለመቆጣጠርና ተጠያቂነትን ለማስፈን እየተሰራ ነው ብለዋል። የፀረ ሙስና ኮሚቴው መቋቋሙን ተከትሎም ህዝቡ በንቃት ጥቆማ የሚሰጥበትን አማራጭ በማስፋት በርካታ ጥቆማዎች እየመጡ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም እስካሁን የመጡ ጥቆማዎችን መነሻ በማድረግ በተካሄደ ምርመራና ክስ 136 ሰዎች ላይ ከአንድ ዓመት እስከ 11 ዓመት የሚደርስ የእስራት ቅጣት መተላለፉን ገልጸዋል። የሃረሪ ክልል የስነ-ምግባርና ጸረ ሙሰና ኮሚሽን ኮሚሽነር ካሊድ ኑሪ በበኩላቸው፤ ኮሚሽኑ አባል የሆነበት ኮሚቴ የሃብት ማስመዝገብና ማጣራት፣ በተቋማት ያሉ አሰራሮችን መፈተሽና ምርመራ ማካሄድ ተጠቃሽ ናቸው። ለኮሚቴው እስካሁን የደረሱትን 67 ጥቆማዎች መሰረት በማድረግ 30 መዝገቦችን በመክፈት 11 በሚሆኑት መዝገቦች ላይ ምርመራ መጀመሩን አረጋግጠዋል። በዚህም ወንጀል መፈጸማቻው በተረጋገጡ 25 የስራ ኃላፊዎችና ሙያተኞች ላይ እርምጃ መወሰዱን ገልጸዋል። የጋምቤላ ክልል የስነ-ምግባርና ጸረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳይመን ቶሪያል፤ ክልሉ በመሬት፣ በንግድና በነዳጅ ግብይት ከፍተኛ የሙስና ወንጀል እንደሚፈጸምበት ጠቅሰዋል። በመሆኑም የፀረ ሙስና ኮሚቴ ተቋቁሞ በይበልጥ ለሙስና ተጋላጭ የሆኑ ዘርፎች ላይ የምርመራና የልየታ ስራ ከማካሄድ ጎን ለጎን ጥቆማዎችን መነሻ በማድረግ የምርመራ ስራ እያከናወነ ነው ብለዋል። በተለይ በነዳጅ ግብይት ላይ ባደረገው ምርመራ 15 በርሜል ነዳጅ በህገ-ወጥ መልኩ ሊወጣ ሲል መያዙንና ወንጀለኞቹን ለህግ ማቅረብ መቻሉን ነው ኮሚሽነሩ ያስረዱት። በክልሉ የነዳጅ ግብይቱ ላይ የአሰራር ማሻሻያ በማድረግ ረገድ ኮሚቴው የጎላ ሚና እንደነበረው አንስተዋል። ህዝቡ ሙስናን በማጋለጥ ረገድ የጀመረውን የጥቆማ መስጠት ተግባር አጠናክሮ እንዲቀጥል ኮሚሽነሮቹ ጠይቀዋል።
በመዲናዋ ባለቤት አልባ ውሾች ለሰውና ለእንስሳት ጤና እክል እየፈጠሩ መሆኑ ተገለጸ
Jun 3, 2023 52
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ) ፦ በአዲስ አበባ ባለቤት አልባ ውሾች እየተበራከቱና በሰውና በእንስሳት ላይ የጤና እክል እያደረሱ እንደሚገኝ ተገለጸ። የእብድ ውሻ በሽታ (ሬቢስ) በቀላሉ ወደ ሰው የሚተላለፍና ገዳይ በሽታ ሲሆን መድኃኒትም እንደሌለው መረጃዎች ይጠቁማሉ ። በሽታው ከውሻ ወደ ሰው የሚተላለፍ ሲሆን በወቅቱ ሕክምና ካልተደረገለት ለሞት የሚዳርግ ነው። በሽታው የመከላከያ ክትባት እንዳለው ቢነገርም በመዲናዋ ካሉት ውሾች ብዛት አንጻር ክትባት የመስጠቱ ስራ በተፈለገው ልክ ተደራሽ እንዳልሆነም ይገለጻል፡፡ በአዲስ አበባ ባለቤት አልባ ውሾች መበራከታቸውን ተከትሎ በሰውና በእንስሳት ከፍተኛ የጤና እክል በማድረስ ላይ መሆናቸውን ኢዜአ ያነጋገራቸው ታካሚዎችና የህክምና ባለሙያዎች ይገልጻሉ። ከታካሚዎቹ መካከል ምስላቸው እንዳይቀረጽ በመጠየቅ አስተያየታቸውን የሰጡት አቶ ቴዎድሮስ ሲሳይ በእብድ ውሻ ተነክሰው ሕክምና እየተከታተሉ መሆኑን ይናገራሉ። ባለቤት አልባ ውሾች ከመንገድ ላይ ባለፈ በአንዳንድ ተቋማት አካባቢም መታየት መጀመራቸውን ጠቁመው የሚመለከተው አካል ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ይላሉ። ሌላው ታካሚ አቶ ደምስ መረጋ፤ በቀን ስራ የሚተዳደሩ ሲሆን ለስራ በሚንቀሳቀሱበት ወቅት በእብድ ውሻ እንደተነከሱ ያነሳሉ። ታካሚው ባላቸው የጤና መድህን መታወቂያ አደጋው እንደደረሰባቸው ለበሽታው ክትባት ማግኘት አለመቻላቸው እንዳሳዘናቸው ገልጸው በአሁኑ ወቅት ግን ሕክምናውን እየተከታተሉ መሆኑን ገልጸዋል። በአፍንጮ በር ጤና ጣቢያ የጤና መድህን አገልግሎት ቡድን መሪ አቶ ታሪክ ተስፋዬ፤ ለእብድ ውሻ በሽታ ክትባት ለማግኘት በመዲናዋ ከሚገኙ 11 ጤና ጣቢያዎች ታካሚዎች ወደ ተቋሙ እንደሚላኩ ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የጤና መድህን አገልግሎት በጤና ጣቢያ ደረጃ አገልግሎት የሚሰጠው በተመዘገቡበት አካባቢ ብቻ መሆኑን አመልክተዋል። በሆስፒታል ደረጃ ደግሞ በመረጃ ቋት የተሳሰረ ስርዓት ያለ በመሆኑ የጤና መድህን አባል የሆኑትን በመለየት የእብድ ውሻ በሽታን ጨምሮ ሌሎች ሕክምናዎች በነጻ እንደሚሰጡ ጠቁመዋል። የአፍንጮ በር ጤና ጣቢያ የድንገተኛ ሕክምና ክፍል ኃላፊ መቅደስ ኃይሉ የእብድ ውሻ በሽታ (ሬቢስ) ታካሚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ይገልጻሉ። በአብዛኛውም ተጎጂ እየሆኑ ያሉት ደግሞ የገቢ አቅማቸው አነስተኛ የሆኑና የጎዳና ተዳዳሪ ዜጎች መሆናቸውን አመልክተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሙሰማ ጀማል፤ በበኩላቸው በመዲናዋ የሚገኙትን የባለቤት አልባ ውሾች ቁጥር ለመቀነስ ውሾችን እንዳይወልዱ የማምከንና የመከተብ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። እስካሁን ባለው ሂደትም በመዲናዋ ከ16 ሺህ በላይ ባለቤት አልባ ውሾችን መከተባቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለየ መልኩ በመዲናዋ በሽታው በተከሰተባቸው አካባቢዎች ውሾችን የመከተብና ለጤና ስጋት አለመሆናቸውን የማረጋገጥ ስራ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። የመዲናዋ ነዋሪዎች ውሾቻቸውን በዓመት አንድ ጊዜ የማስከተብና የመንከባከብ ግዴታቸውን እንዲወጡ ምክትል ኮሚሽነሩ ጥሪ አቅርበዋል። በአዲስ አበባ የእብድ ውሻ በሽታ ክትባት በሶስት ጤና ጣቢያዎች ብቻ እንደሚሰጥም መረጃዎች ያመለክታሉ።
የእምነት ቤቶች ክብር፤ ሰላምና ደህንነት እንዲጠበቅ ሁሉም ወገን የድርሻውን ሊወጣ ይገባል - የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ
Jun 2, 2023 62
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ) ፦ የእምነት ቤቶች ክብር፤ ሰላምና ደህንነት እንዲጠበቅ ሁሉም ወገን የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ሲል የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ገለጸ። የኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ መግለጫ ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል። በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ ከተማ በአንዋር መስጅድ የጁምአ ሰላት ከተሰገደ በኋላ በሸገር ከተማ አስተዳደር ስለፈረሱ መስጅዶች ተቃውሞ ለማሰማት የተደረገውን ሙከራ ተከትሎ በተፈጠረው ግጭትና በተወሰደው የኃይል እርምጃ በሰዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰ እየወጡ ያሉ መረጃዎች ይጠቁማሉ። በተመሳሳይ ባለፈው ሳምንትም ግንቦት 18 ቀን 2015 ዓ.ም በአዲስ አበባ በታላቁ አንዋር እና በኑር (በኒን) መስጅዶች ከጁምአ ሰላት በኋላ በተፈጠረው ተቃውሞና በጸጥታ ኃይሉ የተወሰደው ያልተመጣጠነ እርምጃ ምክንያት ሁለት ሰዎች የሞቱ ሲሆን በርካታ ቁጥር ያላቸው ሙስሊሞችም ከባድና ቀላል አካላዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል። ስለሞቱት ወገኖቻችን ጉባኤው የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን እየገለፀ ለሟቾች ቤተሰቦች ወዳጅ ዘመዶች ሁሉ መጽናናትን ይመኛል፤ በተጨማሪም በዕለቱ የአካልና የሥነ ልቦና ጉዳት ለደረሰባቸው ሁሉ ፈጣን ፈውስን እንዲያገኙ ጉባኤያችን ልባዊ ምኞቱን ይገልፃል። በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያንም በምዕራብ ጎጃምና በአርሲ ሀገረ ስብከት በሚገኙ ሁለት አጥቢያዎች ላይ ደረሰ ስለተባለው ጉዳት እየተጣራ እንደሚገኝ የቤተ ክርስቲያኒቱ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ በይፋዊ የፊስ ቡክ ገጹ ያወጣው መረጃ ይጠቁማል። መስጅዶች እና አብያተ ክርስቲያናት የአማኞች የሃይማኖታዊ፣ የመንፈሳዊ እና የሞራላዊ ዕሴቶች የሚገነባባቸው ዋነኛ ማዕከላት ከመሆናቸውም በላይ የምዕመናን ልዩ ምልክቶች እንደሆኑ የሚታወቅ ሲሆን አማኞችም ከእምነት ተቋማትና ከቤተ እምነቶቻቸው ጋር ያላቸው መንፈሳዊና ስሜታዊ ትስስርም ጠንካራ ነው። ከዚህ አንጻር በአዲሱ በሸገር ከተማ አስተዳደር በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ መስጅዶችና የእምነት ቤቶች ሕጋዊነት ጋር በተያያዘ በመፍረሳቸው ሙስሊሙን ህብረተሰብ አስቆጥቷል። ከዚህ አንፃር ከመነሻው ጀምሮ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት ችግሩ በዘላቂነት እንዲፈታ ከፍተኛ ጥረት ሲያደርግ እንደቆየ የሚታወቅ ሲሆን በተለይም ባለፈው ሳምንት የደረሰውን ጉዳት ተከትሎ ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት በመስጠት ዘጠኝ አባላት ያሉት ኮሚቴ በማቋቋም ከመንግስት ጋር እየተነጋገር እንደሆነ መግለጫ በመስጠት የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳይ ከፍተኛ ምክር ቤት ሕዝበ ሙስሊሙ ዱአ እያደረገ በትዕግስት እንዲጠባበቅ ማሳሰቡ ይታወሳል። ይሁን እንጅ መሪ ተቋሙ ያስተላለፈው ማሳሰቢያ እንደተጠበቀ ሆኖ በዛሬው እለት ማለትም ግንቦት 25 ቀን 2015 ዓ.ም ከጁምዓ ሰላት በኋላ ሁከትና አለመረጋጋት የተከሰተ ሲሆን የጸጥታ ኃይሉ በወሰደው እርምጃ ጉዳት መድረሱ በእጅጉ ያሳዝናል። ስለሆነም የሕዝበ ሙስሊሙ ብቸኛ መሪ ተቋም የሆነው የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ከመንግስት አካላት ጋር የጀመረው ውይይት እስኪጠናቀቅ ሕዝበ ሙስሊሙ በትዕግስት እንዲጠብቅ፣ በተመሳሳይ መንግስትም በተለይም የጸጥታ ኃይሉ የዜጎችን ሰላምና ደህንነት የማስጠበቅ ተግባሩን በከፍተኛ ጥንቃቄና ሆደ ሰፊነት እንዲያከናውን ጉባኤያችን በአጽንኦት እያሳስበ ሁሉም ወገን የመስጅዶችንና የቤተ እምነቶችን ክብር፣ ሰላምና ደህንነት በመጠበቅ የእምነት ቤቶች የተቋቋመበትን ዓላማና ተልዕኮ ለመፈጸም የሚቻልባቸው ቅዱስ ስፍራነታቸው የማክበርና የማስከበር ኃላፊነቱን እንዲወጣ እንጠይቃለን። ፈጣሪ ኢትዮጵያን ይባርክ
ከፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ-ኃይል የተሰጠ መግለጫ
Jun 2, 2023 82
ህዝበ ሙስሊሙ ለሀገራችን ሰላምና ደህንነት መረጋገጥ ጽኑ እምነት ያለው፣ ሀገር እየጠበቀ፣ እየገነባ እና የራሱን ድርሻ እያበረከተ መሆኑ ይታወቃል። ሰሞኑን መስጅዶች ፈርሰዋል በሚል ምክንያት በተፈጠረው ሁከትና ብጥብጥ በሰው ህይወትና ንብረት ላይ ጉዳት የደረሰ ቢሆንም የፀጥታ አካላት የከፋ ጉዳት እንዳይደርስ መስዋዕትነት ከፍለው የከተማውን ሰላም ማረጋጋታቸው የሚታወቅ ነው። ሌላ ተጨማሪ ጉዳት እንዳይደርስም የአዲስ አበባ ፖሊስ የከተማውን ሰላምና ደህንነት ለማወክ የሚንቀሳቀሱ ቡድኖች ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ በሰጠው መግለጫ ማሳሰቡ ይታወሳል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ግንቦት 25 ቀን 2015 ዓ.ም በአዲስ አበባ በሁሉም ክፍለ ከተሞች በሚገኙ መስጅዶች የተካሄደው የጁምአ ሶላት በሰላም ተጠናቋል። የኢትዮጵያ እና የአዲስ አበባ ከተማ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤቶች ያስተላለፉትን ሰላማዊ መልዕክት በመተላለፍ በታላቁ አንዋር መስጅድ የጁምዓ ሶላት በሰላም ተጠናቆ ህዝብ ሙስሊሙ እየተመለሰ ባለበት ሁኔታ ሀይማኖትን ሽፋን በማድረግ ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓቱን ለማፍረስ የሚንቀሳቀሱ የሴራ ቡድኖች የሰላቱን ሰላማዊ ሥነ-ሥርዓት ለማስከበር በተሰማሩ የፀጥታ አካላት ላይ ጉዳት ለማድረስ በተነሳ ረብሻ የሦስት ሰዎች ህይወት ሲያልፍ በተወሰኑ ሰዎች ላይ የአካል ጉዳት ደርሷል። በንብረት ላይም እስከ አሁን ግምቱ ያልተወቀ ኪሳራ የደረሰ ሲሆን ለፀጥታ ሥራ በተሰማሩ 63 የፖሊስ አመራር እና አባላት ላይ ቀላል እና ከባድ የአካል ጉዳት የደረሰ መሆኑን የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ-ኃይል አስታውቋል። ፀረ-ሰላም ኃይሎች የእምነቱ ተከታዮች በህጋዊ መንገድ ያቀረቡትን ጥያቄ በመጥለፍ የራሳቸውን እኩይ ዓላማ ለማሳካት ረብሻውን ወደ ሌሎች አካባቢዎች ለማዛመት ያደረጉት ጥረት የፀጥታ ኃይሉ፣ ህዝበ ሙስሊሙ እና የሀይማኖቱ አባቶች በጋራ በመሆን ባደረጉት ርብርብ መቆጣጠር ተችሏል፡፡ ግብረ-ኃይሉ የከተማውን ብሎም የሀገራችንን ሠላምና ደህንነት ለማስከበር የጀመረውን ህግ የማስከበር ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል እየገለፀ የደረሰውን አጠቃላይ ጉዳት እና በህገ-ወጥ ተግባሩ ላይ የተሳተፉ ፀረ-ሰላም ኃይሎች ላይ የጀመረውን ምርመራ አጠናክሮ በመቀጠል በቀጣይ ውጤቱን ለህዝቡ ይፋ እንደሚያደርግ አስታውቋል። ሰላም የሁሉም የእምነት ተቋማት የአስተምሮታቸው መሠረት በመሆኑ ህዝበ ሙስሊሙ የሚያነሳውን ማንኛውንም ጥያቄ በህግ አግባብ በሰላማዊ መንገድ ማስተናገድ የሚቻልበት ሥርዓት መኖሩን በመገንዘብ ለፀረ-ሠላም ኃይሎች መጠቀሚያ ሳይሆን የፀጥታ አካላት የከተማውን ሰላምና ደህንነት ለመጠበቅ የሚያደርጉትን ጥረት በመደገፍ ህዝበ ሙስሊሙ የዜግነት ድርሻውን እንዲወጣ የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ-ኃይሉ ጥሪውን ያቀርባል። የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ-ኃይል ግንቦት 25 ቀን 2015 ዓ.ም አዲስ አበባ
በኢትዮጵያ የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ማደግ አለበት - የፌዴራል ፍትህና ህግ ኢንስቲትዩት
Jun 2, 2023 74
ደሴ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ )፡- በኢትዮጵያ የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ማደግ እንዳለበት የፌዴራል ፍትህና ህግ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ዘላቂ ሰላም፣ ሰብዓዊ መብትና በሀገራዊ ምክክሩ አበይት ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ጉባኤ በወሎ ዩኒቨርሲቲ እየተካሄደ ነው፡፡ በውይይቱ ላይ የፌዴራል የፍትህና ህግ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ምትኩ ማዳ እንደገለጹት በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ በቅንጅት መስራት ያስፈልጋል፡፡ ኢንስቲትዩቱም የህግ የበላይነት በሁሉም አካባቢዎች እንዲረጋገጥ የፍትህ ዘርፉን በጥናት፣ በስልጠናና አቅም ግንባታ እየደገፈ እንደሚገኝ ተናግረዋል። አገራዊ ምክክሩ ውጤታማ ሆኖ በኢትዮጵያ አሰተማማኝ ሰላም እንዲሰፍን የተጀመረውን ጥረት እንደሚደግፉም አስረድተዋል። የህግ የበላይነት ተረጋግጦ የዜጎች ሰብዓዊ መብት እንዲከበር፣ ፍትህ እንዲሰፍን የሁሉም ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ መጎልበት አለበት ነው ያሉት። የወሎ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶክተር መንገሻ አየነ በበኩላቸው ዘላቂ ሰላም፣ አንድነትና ልማት እንዲረጋገጥ ዩኒቨርሲቲው የድርሻውን እየተወጣ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ለዚህም የጋራ ባህልና እሴቶቻችን በማጎልበት፣ ምሁራን ለህብረተሰቡ ግንዛቤ እንዲፈጥሩና አገራዊ ምክክሩ አሳታፊ እንዲሆን ከፌዴራል ተቋማት ጋር ጭምር እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሶፊ መምህሩ ዶክተር ዳኛቸው አሰፋም እንዲሁ በዚህ ወቅት ሁሉም ህዝብ ከግል ጥቅሙ ይልቅ ሀገርን ማስቀደም አለበት ብለዋል። ''ሁሉም ዜጋ ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም፣ አንድነትና ልማት በጋራ መረባረብ ይኖርበታል'' ያሉት ዶክተር ዳኛቸው ምሁራንም ህዝብና መንግስትን የሚያቀራርቡ ጥናቶችን ማካሄድ እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። ''በብሄራዊ ምክክሩ ጠቀሜታ ዙሪያ ለህዝቡ ግንዛቤ በመፍጠር የድርሻችንን መወጣት አለብን'' ነው ያሉት። ከ10 በላይ የጥናት ስራዎች በሚቀርቡበት የውይይት መድረክ ላይ ከፍተኛ አመራሮች፣ ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የተውጣጡ ምሁራንና ሌሎችም እየተሳተፉ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የብዝሃነት ሚኒስትር ጋር ተወያዩ
Jun 2, 2023 99
አዲስ አበባ ኢዜአ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ):-የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትሪያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የብዝሃነት ሚኒስትር ሼህ ናህያን ሙባረክ አል ናህያን ጋር ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በጥር 2015 በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የስራ ጉብኝት ባደረጉበት ወቅት በአቡዳቢ የአገሪቱ መንግስት በሰጠው 17 ሺህ 682 ካሬ ሜትር ላይ እየተሰራ የሚገኘውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መጎብኘታቸው ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ለተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መንግስት ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን የዋና የቤተ ክርስቲያኑ ግንባታ እስኪጠናቀቅ ለጊዜው መገልገያ የሚሆን ቤተ ክርስቲያን ግንባታ እየተጠናቀቀ መሆኑንም በወቅቱ ገልጸው ነበር። ብፁዕነታቸው በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መዲና አቡዳቢ ለሚገነባው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ሕንጻ መሰረት ድንጋይ ለማኖር እንዲሁም የመቃረቢያ ቤተ ክርስቲያን መርቀው ለመክፈት ትናንት ዩኤኢ መግባታቸው ይታወቃል። አቡነ ማትያስ ዛሬ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የብዝሃነት ሚኒስትር ሼህ ናህያን ሙባረክ አል ናህያን ጋር ውይይት አድርገዋል። ሼህ አል ናህያን ቅዱስ ፓትርያርኩ ለጉብኝት ወደ አቡዳቢ በመምጣታቸው ክብር እና ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸው ጉብኝታቸው በኢትዮጵያና በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መካከል ያለውን የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ለማጠናከር አዎንታዊ ሚና ይጫወታል ብለዋል። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በበኩላቸው የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መንግስት ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ሕንጻ መገንቢያ ለሰጠው መሬት ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን ለተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ሕዝብ እና መሪዎች ጤናና ብልጽግናን ተመኝተዋል:: ከውይይቱ በኃላ የብዝሃነት ሚኒስትሩ ለቅዱስነታቸው እና ለልዑካን ቡድናቸው የምሳ ግብዣ አድርገዋል። በስነ ስርዓቱ ላይ በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ኡመር ሁሴን እንዲሁም የበርካታ አገራት አምባሳደሮች እና የተለያዩ ቤተ እምነቶች ተወካዮች ተገኝተዋል።
በጎ አስተሳሰብ ይዞ ለአገር ግንባታ የሚተጋ ትውልድ ለመፍጠር ሁሉም የድርሻውን አስተዋጽኦ ሊያበረክት ይገባል- ዶክተር ፋንታ ማንደፍሮ
Jun 2, 2023 62
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ):- በጎ አስተሳሰብ ይዞ ለአገር ግንባታ የሚተጋ ትውልድ ለመፍጠር ሁሉም የድርሻውን አስተዋጽኦ ሊያበረክት እንደሚገባ የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ፋንታ ማንደፍሮ ተናገሩ። ዓመታዊው አገር አቀፍ የመመሰጋገንና የመደናነቅ ቀን በሚሊኒየም አዳራሽ ተካሂዷል። ቀኑ የትምህርት ሚኒስቴር፣ ሰላም ሚኒስቴር፣ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት እና ቅን ኢትዮጵያ ማህበር በጋራ ያዘጋጁት ሲሆን ተማሪዎች፣መምህራንና ወላጆች የሚመሰጋገኑበት መርሐ-ግብር ተካሂዷል። በመርሐ-ግብሩ ላይ የሃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ወላጆች እና ከተለያዩ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ ተማሪዎች ታድመዋል። የዝግጅቱ ዓላማ በተለይም ምስጋናን ባህል ማድረግ፣ በትውልዱ ዘንድ ጥላቻንና መለያየት እንዳይኖር በትኩረት እንዲሰራበት ለማሳሰብ ያለመ መሆኑ ተገልጿል። በዚህ ዝግጅት ላይ ተማሪዎች መምህራኖቻቸውንና ወላጆቻቸውን የሚያመሰግኑበት ኪነ-ጥበባዊ ስራዎችና ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን ቀርበዋል። የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ፋንታ ማንደፍሮ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ ትውልዱ ምስጋናንና መልካም ስነ-ምግባርን ባህል እንዲያደርግ የአስተማሪዎች፣ ወላጆች እና የትምህርት ዘርፉ ላይ ያሉ ባለድርሻ አካላት ድጋፍ ወሳኝ ነው ብለዋል። የትምህርት ሚኒስቴር ከመደበኛ ትምህርት ጎን ለጎን ግብረ-ገብነት በተማሪዎች ዘንድ እንዲጎለብት በስርዓተ ትምህርት አካቶ እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። ቀጣዩ ትውልድ አገር የሚገነባ እንዲሆን ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት በትብብር እየሰራ መሆኑን ገልጸው፤ ለተመሳሳይ ዓላማ መሳካት እየሰራ ካለው ቅን ኢትዮጵያ ማህበር ጋር በበርካታ ጉዳዮች ላይ በጋራ እየተሰራ እንደሆነ ተናግረዋል። የመምህራን አሻራ ያላረፈበት መሐንዲስ፣ ተመራማሪ እና ሳይንቲስት የለም ያሉት ሚኒስትር ደኤታው ለመምህራን ክብርና ምስጋና ብናቀርብ ሲያንስ እንጂ አይበዛም ሲሉ ገልጸዋል። እንደ ዶክተር ፋንታ ገለጻ መመሰጋገንና መደናነቅን ባህል የሚያደርግ ትውልድ ለመፍጠር ከታች ጀምሮ ትውልዱን ማነጽ ላይ ሊሰራ ይገባል ነው ያሉት። የሰላም ሚኒስትር ደኤታ ዶክተር ስዩም መስፍን በበኩላቸው "ምስጋና ለሰጪው የማይከብድ ለሚቀበለው ግን ከስጦታዎች ሁሉ የላቀ ዋጋ ያለው ስጦታ ነው" ሲሉ ገልጸዋል። ምስጋና አንድን ሰው የበለጠ የሚያተጋና የሚያነሳሳ አለፍ ሲልም ለዘላቂ እድገት መረጋገጥ አዎንታዊ ሚና ያለው መሆኑን አመልክተዋል። ሰላምን የሚያስቀድም ትውልድ በበጎ እይታ የሚመራ ትውልድ የመፍጠር ጉዳይ በአንድ ጀንበር የሚሳካ አይደለም ያሉት ዶክተር ስዩም ለዚህም ተከታታይ ሥራ ይፈልጋል ብለዋል። በዚህ ረገድም የመሰል የመመሰጋገን፣የመደናነቅና የመከባበር ሁነቶች ትልቅ ሚና አለው ሲሉ ነው የገለጹት። የቅን ኢትዮጵያ ማህበር መስራች ዶክተር ቶሎሳ ጉዲና እንደሚሉት፤ ማህበሩ በመልካም ስነ-ምግባር ታንጾ ለአገር ጠቃሚ ትውልድ የመፍጠር ዓላማን ለመደገፍ የተቋቋመ ነው። ማህበሩ በዚህ በኩል የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ገልጸው ወላጆች፣መምህራንና ሌሎችም የሚመለከታቸው አካላት የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት በላቀ ደረጃ እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። ጥላቻ፣ መለያየት፣ዘረኝነትና ክፋት በትውልዱ ዘንድ ቦታ እንዳይኖረው በማድረግ ረገድ የወላጆች ሚና ከፍ ያለ በመሆኑ ወላጆች ይሄን ሚናቸውን በአግባቡ መውጣት እንደሚገባቸው አመልክተዋል። ተማሪዎች የነገ ተረካቢዎች እንደ መሆናቸው መጠን አንድነትና ሕብረት ላይ ማተኮር እንዳለባቸው ነው ዶክተር ቶሎሳ ያስረዱት።
የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች የፈጠራ ሥራዎቻቸው ለህዝብ እንዲያስተዋውቁ ድጋፍ ሊደረግላቸው ይገባል -ቱሪዝም ሚኒስቴር
Jun 2, 2023 39
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፦የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች የፈጠራ ሥራዎቻቸውን በስፋት ለህዝብ እንዲያስተዋውቁ ባለድርሻ አካላት ድጋፍ ሊያደርጉላቸው እንደሚገባ ቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ስለሺ ግርማ ተናገሩ። 14ኛው ከተማ አቀፍ የኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል በአዲስ አበባ ከተማ በተለያዩ ዐውደ ርዕይ እና ሥነ-ጥበባዊ ክዋኔዎች መቅረብ ጀምረዋል። የኪነ-ጥበብ መድረኩም "በሥነ- ጥበባት ሕብራዊ መልክ የተዋበች ኢትዮጵያ'' በሚል መሪ ቃል ከግንቦት 25 እስከ 27 ይካሄዳል። ለሶስት ቀናት በሚቆየው በዚሁ ፌስቲቫል በዛሬው ውሎው የተለያዩ የሥነ-ጽሑፍ፣ የኪነ- ጥበብና ሌሎች መሰል ሥራዎች ቀርበውበታል። ቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ስለሺ ግርማ በማስጀመሪያው ወቅት እንዳሉት በኪነ-ጥበብና ሥነ-ጥብብ ዘርፍ የተሰማሩ አካላት የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ለሕዝብ እንዲያቀርቡም የኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል ፋይዳቸው የጎላ ነው እንደሆነ ገልፀዋል። ኪነ-ጥበብን ወደ ኢኮኖሚ አመንጪነት ለማሳደግ ፌስቲቫሎችን በጥራት ማዘጋጀት አስፈላጊ ነው ብለዋል ። ስለሆነም ከተማ አቀፍ የኪነ-ጥበብ መድረኮች መዘጋጀታቸው በሀገር አቀፍ ደረጃ በመንግሥት የተያዘውን የቱሪዝም ልማት የሚደግፍና ኢኮኖሚያዊ አቅምን የሚያሳድግ ነው ብለዋል። ይህንንም ለማጠናከር የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ለህዝብ እንዲያስተዋውቁ ባለድርሻ አካላት ድጋፍ ሊያደርጉላቸው ይገባል ብለዋል። የአዲስ አበባ ባህል፣ ኪነ-ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ የኪነ-ጥበብ ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ሠርፀ ፍሬስብሐሃት በበኩላቸው መድረኩ በከተማው ያለውን የኪነ-ጥበብ ሀብቶች አጉልቶ ለማሳየት የሚረዳ ነው ብለዋል። "ለጥበብ ሥራዎች የክወና መድረክ ከማግኘት በላይ ትልቁ አንቀሳቃሽ ኃይል የሕዝብ እይታና አድናቆት ነው" ያሉት ምክትል ቢሮው ኃላፊ ሥነ-ጥበባዊ ፈጠራዎችንና ፌስቲቫሎችን ማመቻቸት አስፈላጊ የሚሆነውም ለዚህ ነው ብለዋል። ከአዲስ አበባ ጋር ተመሳሳይ ተሞክሮዎችን የሚጋሩ የዓለም ከተሞች ዓመቱን ሙሉ በከፍተኛ ጥራት የሚዘጋጁትን የኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል ዘርፉን ወደ ኢኮኖሚ አመንጪነት ለመቀየር ከፍተኛ እገዛ እንዳደረገላቸው ገልጸዋል። የሚመለከታቸው ይህንን እንደ አገር በተሞክሮነት ሊወስዱት ይገባል ያሉ ሲሆን ባለሃብቶች በሚዘጋጁ ፌስቲቫሎች ላይ በስፋት እንዲሰማሩ ጥሪ አቅርበዋል።
በመዲናዋ በዘንድሮ የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ1 ሚሊየን በላይ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው
Jun 2, 2023 52
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ)፡- በመዲናዋ በዘንድሮ የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሃ ግብር ከ1 ሚሊየን በላይ የኅብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ገለጸ። የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽነር አብርሃም ታደሰ ለኢዜአ እንደገለፁት በመዲናዋ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እየተጠናከረ መጥቷል። በዘንድሮ የ2015 የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎትም በመዲናዋ 2 ሚሊየን የሚጠጉ በጎ ፈቃደኞች በተለያዩ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት አይነቶች ይሳተፋሉ ብለዋል። በጎ ፈቃደኞቹ በቤት እድሳት፣ በደም ልገሳ፣ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርና በሌሎችም ዘርፈ ብዙ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተሳትፎ እንደሚኖራቸው ገልጸዋል። ለአብነትም ከ270 በላይ ቤቶች ግንባታና እድሳት ሥራ መጀመሩን ጠቁመው፤ በሌሎች መስኮች በጎ ፈቃደኞቹ ሥራቸውን አጠናክረው መቀጠላቸውንም ተናግረዋል። በግንቦት ወር 2015 ዓ.ም ተጀምሮ እስከ ቀጣይ ዓመት መስከረም በሚዘልቀው በዚህ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በመዲናዋ የሚገኙ ከ1 ሚሊየን በላይ የኅብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሃ - ግብሩ ውጤታማ እንዲሆን በጎ ፈቃደኞች ባላቸው ጉልበት፣ እውቀትና ገንዘብ ኅብረተሰባቸውን የሚያገለግሉበት ሁኔታዎች መኖራቸውንም አብራርተዋል። ኮሚሽኑ የሚሰሩ የበጎ ፈቃድ ተግባራት ተጨባጭ ለውጥ እንዲያመጡ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተሳትፏቸውን እንዲያጎለብቱ ለማድረግ የጀመረውን ሥራ አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በከተማው ለሚከናወኑ የበጎ ፈቃድ ሥራዎች ከግብ እንዲደርሱ የኅብረተሰቡን የነቃ ተሳትፎ የሚጠይቅ በመሆኑ ነዋሪዎች በሚችሉት አቅም የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበርክቱ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። በዘንድሮም ዓመት በአገር አቀፍ ደረጃ 20 ሚሊየን የሚጠጉ በጎ ፈቃደኞች በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የሚሳተፉ መሆናቸውን የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መግለጹ ይታወሳል።
ጂንካ ዩኒቨርሲቲ የመጥፋት አደጋ የተጋረጠበትን የ"ኦንጎታ" ቋንቋ ለመታደግ እየሰራሁ ነው አለ
Jun 2, 2023 52
ጂንካ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ):-በደቡብ ኦሞ ዞን በና ፀማይ ወረዳ በአምስት የብራይሌ ጎሳ አባላት የሚነገረውን እና የመጥፋት አደጋ የተጋረጠበትን የ"ኦንጎታ" ቋንቋን ለመታደግ እየሰራ መሆኑን የጂንካ ዩኒቨርስቲ ገለጸ። በዩኒቨርስቲው የምርምርና የማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ኤሊያስ ዓለሙ ለኢዜአ እንደገለፁት በሀገሪቱ የመጥፋት አደጋ ከተጋረጠባቸው ቋንቋዎች መካከል በደቡብ ክልል የሚገኘው "ኦንጎታ አንዱ ነው። አምስት የጎሳ አባላት ባሉት የብራይሌ ብሔረሰብ አባላት የሚነገረው የ"ኦንጎታ" ቋንቋ ከብሔረሰቡ አባላት ሶስቱ ብቻ በትክክል ቋንቋውን እንደሚናገሩም ተናግረዋል። የቋንቋ ተናጋሪዎቹ እድሜ ከ50 በላይ መሆኑ ደግሞ ቋንቋው የመጥፋት አደጋ እንደተጋረጠበት ማሳያ እንደሆነም ገልጸዋል። በመሆኑም ጂንካ ዩኒቨርስቲ ከአርባ ምንጭ ዩኒቨርስቲ ጋር በመተባበር ቋንቋውን ከመጥፋት አደጋ ለመታደግ ጥረት መጀመሩን አመልክተዋል። በዋናነትም በቋንቋው ላይ ያተኮረ የጥናትና ምርምር ስራ እየተካሄደ መሆኑን ገልጸው፤ በተለይ ቋንቋውን ለማስቀጠል እንዲቻል ከተናጋሪዎቹ ጋር በመተባበር መዝገበ ቃላት ለማዘጋጀት እንቅስቃሴ ተጀምሯል ብለዋል። ይህም ቋንቋውን ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲሸጋገር ሚና እንዳለው አውስተዋል። በእርግጥ የ"ኦንጎታ" ቋንቋ ከየትኛው የቋንቋ ነገድ እንደሚመደብ "እስካሁን አይታወቅም" ያሉት ዶክተር ኤሊያስ፤ ከአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመቀናጀት በቋንቋው ላይ የሚሰራው ጥናት ይህንን ለመመለስና የቋንቋውን ቤተሰብ በሳይንሳዊ መንገድ ለመለየት እንደሚያስችል ተናግረዋል። በጥናቱ በቋንቋውና በባህሉ ውስጥ ያሉ ጠቃሚ እሴቶችና አገር በቀል ዕውቀቶች ጎልተው እንዲወጡና ተሰንደው ለትውልድ እንዲተላለፉ እንደሚደረግም ገልፀዋል። በአውሮፓውያን አቆጣጠር ከ1970 እስከ 1990ዎቹ በተሰሩ ጥናቶች የ"ኦንጎታ" ቋንቋ ተናጋሪዎች 89 ሲሆኑ በ2006 በተካሄደው ጥናት ደግሞ ስምንት ብቻ ቀርተዋል። በአሁኑ ሰዓት አምስት የቋንቋው ተናጋሪዎች ያሉ ሲሆን ከአምስቱ ሶስቱ ብቻ ቋንቋውን በትክክል እንደሚናገሩ አውስተዋል። የደቡብ ኦሞ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ አቶ ማሞ ካይሲ በበኩላቸው የቋንቋ መዳከምና መጥፋት በአንድ ማህበረሰቡ ውስጥ የሚገኙ ታሪካዊ ፣ ባህላዊና ትውፊታዊ ሀብቶችም አብረው እንዲጠፉ ያደርጋል ብለዋል። ይህ እንዳያጋጥም መምሪያው ለመጥፋት የተቃረቡ ቋንቋዎችን ለመታደግ የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከተግባራቱ መካከል ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመተባበር ቋንቋዎቹ በሥርዓተ ትምህርት ውስጥ የሚካተቱበትን ጥናት የማካሄድ ሥራ እንደሚጠቀስ አመላክተዋል። መምሪያው አሁን ላይ የጂንካ ዩኒቨርሲቲን ጨምሮ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን በማስተባበር ለ"ኦንጎታ" ቋንቋ ፊደል እያዘጋጀ እንደሚገኝ ገልፀዋል። በተጨማሪም በባህሉ ውስጥ ያሉ ተረቶች፣ ትውፊቶች፣ ምሳሌያዊ አነጋገሮች እና ባህላዊ መድሐኒት አዘገጃጀት ጥበቦችን የማሰባሰብ እና በመፅሐፍ መልክ እንዲታተሙ የማድረግ ስራ እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ለቋንቋው ፊደል የመቅረፅ ስራው በሂደት ላይ እንደሚገኝ ጠቅሰው ሲጠናቀቅ ቋንቋው በስርዓተ ትምህርት ውስጥ ተካቶ በአፍ መፍቻ ቋንቋነት በአካባቢው ባሉ ትምህርት ቤቶች እንዲሰጥ ይደረጋልም ብለዋል። የጂንካ ዩኒቨርሲቲ እና የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የመጥፋት አደጋ ያጋጠመውን የ"ኦንጎታ" ቋንቋን ለመታደግ ከመምሪያው ጎን በመሆን የጀመሩት የጥናትና ምርምር ስራ ቋንቋውን ለመታደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውም ገልጸዋል። መምሪያው ተባባሪ አካላትን በማስተባበር ቋንቋውን ለመታደግ የሚሰሩ ስራዎች ለስኬት እንዲበቁ አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል ። መምሪያው በዞኑ የሚገኙ የተለያዩ ቋንቋዎች እንዲበለጽጉና የሚጠበቀውን ዕድገት እንዲያሳዩ የተለያዩ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ ገልጸው ለአብነት የአሪ ቋንቋ ፊደል ተቀርጾለት በትምህርት ስርዓት ውስጥ እንዲካተት መደረጉን አንስተዋል።
ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ የምግብ አመራረት ስርዓት እውን እንዲሆን የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ሙያዊ እገዛ ተጠየቀ
Jun 2, 2023 61
አዳማ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ) ደህንነቱ የተረጋገጠና ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ የምግብ አመራረት ስርዓት እውን ለማድረግ የሚደረገውን ጥረት የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች በሙያቸው ማገዝ እንደሚገባቸው የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት አስገነዘበ። ከፌዴራልና ክልሎች የተውጣጡ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች የተሳተፉበትና ጥራት ያለው የምግብ ደህንነት ማረጋገጥ በሚቻልበት ሂደት ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በአዳማ በመካሄድ ላይ ይገኛል። የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ቦንሳ ባይሳ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት የምግብ ደህንነት ማረጋገጥ የሚቻለው ከምርት ሂደት ጀምሮ እስከ አመጋገብ ድረስ ያሉትን ሂደቶች ጥራት መጠበቅ ሲቻል ነው። "ለምግብ ደህንነት መረጋገጥ ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር ይገባናል" ያሉት አቶ ቦንሳ፤ በዚህም ከሚዲያ አካላት ጋር በትብብር ለመስራት የሚያስችል አቅም ለመፍጠር ያለመ መድረክ ተዘጋጅቷል ብለዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ5ኛ ጊዜ በሀገራችን ለ4ኛ ጊዜ የሚከበረውን የምግብ ደህንነት ቀን ምክንያት በማድረግ የምግብ ደህንነት ሳምንት እየተከበረ መሆኑንም ተናግረዋል። በዚህም የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ከእርሻ ስራው ጀምረው እስከ አመጋገብ ድረስ ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ ምግብ እንዲመረት የሚደረገውን ቁጥጥር፣ ክትትልና ድጋፍ ማገዝ እንደሚገባቸው ምክትል ዳይሬክተሩ አስገንዝበዋል። በተለይም ምግቦች ከሚመረቱበት ግብዓትና ፋብሪካዎች ጀምሮ ያለውን የምግብ ደህንነት፣ ቁጥጥርና ክትትሉ ውጤታማ እንዲሆን በባለቤትነትና ከኢንስቲትዩቱ ጋር ሆነው በሙያቸው እንዲያግዙ ለማስቻል ጭምር መድረኩ አስፈልጓል ብለዋል። አክለውም የሀገሪቱን የምግብ ምርቶች ጥራትና ደረጃቸውን ለማስጠበቅ የተዘረጉ አሰራሮች፣ የሕግ ማዕቀፎችና ፖሊሲዎች ውጤታማ እንዲሆኑና የተፈለገው ውጤት እንዲመዘገብ ከሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ ብዙ ይጠበቃል ብለዋል። በኢትዮጵያ የምግብና መድኃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን የምግብ ደህንነት ምዝገባና ፍቃድ ዳይሬክተር አቶ በትረ ጌታሁን በበኩላቸው ወደ ሀገር ውስጥ የሚገቡና የሚወጡ የምግብ ምርቶችን ጥራትና ደህንነት ለማስጠበቅ በሚደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ የሚዲያ አካላት የጎላ ተሳትፎ ሊኖራቸው ይገባል ብለዋል። በዚህም በተለይ የምግብ ምርቶች ጥራትና ደረጃቸውን በማስጠበቅ ላይ በትብብር መስራት አለብን ብለዋል። ዜጎች ደህንነቱ የተጠበቀና ለሰውነት ግንባታ የሚውል የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ ለማስቻል የሚደረገውን ጥረት የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ሊያግዙን ይገባል ነው ያሉት። በመድረኩ የምግብ ደህንነት ማረጋገጥ በሚቻልበት ሂደት ላይ መነሻ የውይይት ጽሁፎችና አሰራሮች ቀርበው ይመክርባቸዋል።
በሐረሪ ክልል ማህበረሰቡን በማስተባበር ሰላምና ፀጥታን የማስከበሩ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ፖሊስ አስታወቀ
Jun 2, 2023 60
ሐረር ግንቦት 25 / 2015 (ኢዜአ) ፡- በሐረሪ ክልል ማህበረሰቡን በማስተባበር ፅንፈኝነትን በመከላከል ሰላምና ፀጥታን የማስከበሩ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ። የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ገናነው ጥበበ ለኢዜአ እንዳመለከቱት፤ የክልሉ ማህበረሰብ አንድነቱን በመጠበቅ በሰላም ጉዳይ ላይ ያገባኛል በሚል በፀጥታ ጥበቃና ህግ ማስከበር ላይ እኩል ተሳትፎ እያደረገ ይገኛል፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተደረገው እንቅስቃሴ በክልሉ የወንጀል ተግባር 12 በመቶ መቀነስ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ የወንጀል ድርጊት ሊቀንስ የቻለውም የክልሉ ህዝብ የሰላሙ ባለቤት በመሆን በማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ አደረጃጀቶች ውስጥ በመሳተፍ በየዕለቱ እያከናወናቸው በሚገኘው የቁጥጥርና ፍተሻ ተግባር መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የሰላምን ስራ በፖሊስ አካላት ብቻ ማረጋገጥ የማይቻል ነው ያሉት ምክትል ኮሚሽነሩ፤ ማህበረሰቡ የፖሊስ አጋር በመሆን የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ በክልሉ የፅንፈኝነት አመለካከትን ቀድሞ ለመከላከልም ተሰሚነት ካላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር በቅርበት በመወያየት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በክልሉ የተጀመረውን የፅንፈኝነትና ፀረ ሰላም እንቅስቃሴን ቀድሞ የመከላከል ስራም ማህበረሰቡን ባሳተፈ መልኩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ምክትል ኮሚሽነር ገናነው ገልጸዋል፡፡ በሐረሪ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ አገልግሎት ዳይሬክተር ምክትል ኮማንደር ታጁ ኡመር፤ ማህበረሰቡ ከፖሊስ ጋር ተቀናጅቶ መስራቱ በሰላም እሴት ግንባታው ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረዋል፡፡ በተለይ ማህበረሰቡ በሰላም አደረጃጀቶች መሳተፉ እርስ በእርስ እንዲተዋወቅና ሰላሙን በጋራ እንዲጠብቅ በማስቻሉ በየአካባቢው ይከሰቱ የነበሩ ወንጀሎች መቀነሱን አመልክተዋል፡፡ ወንጀልን ቀድሞ በመከላከል ብሎም ተፈፅሞ ሲገኝ የህግ ተጠያቂነት እንዲኖር ለማድረግ ዘርፈ ብዙ ተግባራት መከናወናቸውን የገለጹት የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ገለልተኛ አማካሪ ምክር ቤት ስራ አስፈፃሚ አባል አቶ ሲሳይ በቀለ ናቸው። ሐረር የምታወቀው በሰላምና በአብሮነት ብሎም በመቻቻል ነው ያሉት አቶ ሲሳይ ፤ ማህበረሰቡ በሰላም ስራው ላይ መሳተፉ አብሮነቱን ይበልጥ እያጎላው መምጣቱን ተናግረዋል፡፡ በክልሉ የአባድር ወረዳ ነዋሪ አቶ ቡሽራ ያሲን በሰጡት አስተያየት፤ ሰላም ለእያንዳንዱ ማህበረሰብ አስፈላጊ በመሆኑ በፈረቃ በመውጣት የአካባቢያቸውን ሰላም በመጠበቅ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡ በተለይ ሰላምን በፖሊስ ብቻ ማረጋገጥ ስለማይቻል ከፖሊስ ጎን በመሆን ፍተሻ በማካሄድና አጠራጣሪ ሁኔታ ሲያግጥም ጥቆማ በመስጠት በሰላም ግንባታው ላይ ሃላፊነታቸውን እየተወጡ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የሸንኮር ወረዳ ነዋሪ ወጣት ሰለሞን ፍቃዱ ፤ ተሸከርካሪዎች ሥርዓት ጠብቀው እንዲያሽከረክሩ ከማድረግ ባሻገር የባጃጅ ላይ ስርቆትን በመከላከል ላይ እንደሚገኙ ገልጿል፡፡ በተጨማሪም የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴዎችና ሌሎች ወንጀሎችን መከላከል በኮሚኒቲ ፖሊሲንግ አደረጃጀት በትብብር እየሰሩ መሆናቸውን ጠቅሶ፤ የኮንትሮባንድ ቁሶችን በቁጥጥር ስር አውለው ለህግ ማቅረባቸውን ጠቁሟል፡፡ የማህበረሰብ አቀፍ ፖሊስ አገልግሎት ስራ በክልሉ በከተማና በገጠር በየዕለቱ ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አመልክቷል፡፡
በጋምቤላ ክልል የሕጻናት የመቀንጨር ችግርን ለመከላከል በተደረገው ጥረት መሻሻል ታይቶበታል- የክልሉ ጤና ቢሮ
Jun 2, 2023 81
ጋምቤላ ግንቦት 25/2015( ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል በተመጣጠነ ምግብ እጥረት የሚያጋጥመውን የሕጻናት መቀንጨር ችግር ለመከላከል በተደረገው ጥረት መሻሻል መታየቱን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የእናቶች እና ሕጻናት ጤና አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ኡጁሉ ኡሞድ ፤ በክልሉ በተመጣጠነ ምግብ እጥረት የሚቀነጭሩ ሕጻናትን ለመቀነስ በተደረገው ጥረት የመጠነ መቀንጨር ምጣኔን እ.አ.አ በ2000 37 በመቶ የነበረውን ወደ 17 በመቶ ዝቅ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ይህም ከአገር አቀፍ የመጠነ መቀንጨር ምጣኔ ጋር ሲነጻጸር ከግማሽ በላይ በመቀነስ መሻሻል መታየቱን አመልክተዋል። የሚቀነጭሩ ሕጻናት ቁጥር በመቀነስ ረገድ የተገኘው ውጤት በዘርፉ የተጠናከረ ግንዛቤ የመፍጠር ስራ በመከናወኑ እንዲሁም በአካባቢው ማህበረሰብ ጥሩ የአመጋገብ ዘይቤ እና ምቹ የተፈጥሮ ሀብት በመኖሩ ነው ብለዋል። በሌላ በኩል በምግብ እጥረት ምክንያት የሚቀጭጩ ሕጻናት ቁጥር ከፍተኛ መሆኑንና የሚቀጭጩ ሕጻናት ቁጥር 12 ነጥብ 6 በመቶ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህም ከአገር አቀፉ በ5 ነጥብ 6 በመቶ ብልጫ እንዳለው ነው ዳይሬክተሩ ያመለከቱት። በአንጻሩ በክልሉ በምግብ እጥረት የሚቀጭጩ ሕጻናት ቁጥር ከፍተኛ ሊሆን የቻለው በየዓመቱ በወንዞች ሙላት ምክንያት በሚከሰት የጎርፍ አደጋ መፈናቀልና ሌሎች ምክንያቶች እንደሆነ ጠቅሰው ችግሩን ለማቃለል እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። የጤና ቢሮው እንደ አገር እ.አ.አ በ2025 በተመጣጠነ ምግብ እጥረት የሚታየውን የሕጻናት መቀንጨር ችግር ለመቀነስ የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር በመታገዝ እቅዱን ለማሳካት እየሰራ ነው ብለዋል። የጋምቤላ ክልል የኢታንግ ልዩ ወረዳ የስርዓተ ምግብ አስተባባሪ አቶ ማሞ አበበ በበኩላቸው፤ በተመጣጠነ ምግብ እጥረት የሚቀነጭሩ ሕጻናትን ቁጥር ለመቀነስ ለእናቶች በተግባር የተደገፈ ግንዛቤ የማሳደግ ስራ እየተከናወነ መሆኑን አመልክተዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የወረዳው ነዋሪዎች በበኩላቸው የባለሙያዎችን ምክር ተቀብለው እየተገበሩ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ለሕጻነት ልጆቻቸው የተለያዩ የምግብ ዓይነቶችን አመጣጥነው እየመገቡና እያስከተቡ መሆኑን አመልክተዋል። ቀደም ሲል በምዕተ ዓመቱ የልማት ግቦች ተካቶ ቀጥሎም በሰቆጣ ቃል ኪዳን ስምምነት በተመጣጠነ የምግብ እጥረት የሚቀነጭሩ ሕጻናትን ቁጥር ለመቀነስ እንደ አገር ግብ ተቀምጦ እየተሰራ ይገኛል።
14ኛው ከተማ አቀፍ የኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል መካሄድ ጀመረ
Jun 2, 2023 56
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፦14ኛው ከተማ አቀፍ የኪነ-ጥበብ ፌስቲቫል በአዲስ አበባ መካሄድ ጀመረ። ፌስቲቫሉ '' በሥነ- ጥበባት ሕብራዊ መልክ የተዋበች ኢትዮጵያ'' በሚል መሪ ሀሳብ ከግንቦት 25 እስከ 27 ይቆያል። በከተማ ደረጃ ለ14ኛ ጊዜ በሚካሄደው ፌስቲቫል የሥነ- ጥበብ እንቅስቃሴዎች፣ የተለያዩ ውድድሮች፣ ዐውደ ርዕይ እና ሥነ-ጥበባዊ ክዋኔዎች እየቀረቡ ይገኛሉ። የአዲስ አበባ ባህል፣ ኪነ-ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ የኪነ-ጥበብ ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ሠርፀ ፍሬስብሐሃት በማስጀመሪያው መርሃ ግብሩ ላይ እንደተናገሩት ፌስቲቫሉ በከተማዋ ያሉትን የኪነ-ጥበብ ሀብቶች አጉልቶ ለማሳየት የሚረዳ ነው። የቢሮው ሃላፊ የከተማዋ ነዋሪ፣ የኪነ-ጥበብ አድናቂዎች እና የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች እንዲሁም መገናኛ ብዙሃንም በፌስቲቫሉ ላይ እንዲታደሙ ጥሪ አስተላልፈዋል። በፌስቲቫሉ ላይ በከተማዋ የሚገኙ የሥነ- ጥበብ ተቋማት፣ ቴአትር ቤቶች፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሥነ ጥበብ ትምህርት ቤቶች፣ የውጭ ዲፕሎማቶች፣ የሃይማኖት ተቋማት ፣ የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣ የአንደኛ እና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንዲሁም የሙያ ማህበራት ተሳትፈዋል።
ወይዘሪት ፀጋ በላቸውን በመጥለፍ ወንጀል የተጠረጠሩ 11 ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው ነው- ቢሮው
Jun 2, 2023 59
ሀዋሳ ግንቦት 25 /2015 (ኢዜአ):- ወይዘሪት ፀጋ በላቸውን በመጥለፍ ወንጀል የተጠረጠሩ 11 ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ እየተደረገባቸው መሆኑን የሲዳማ ክልል ሰላምና ጸጥታ ቢሮ አስታወቀ። የሲዳማ ክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ሃላፊ አቶ አለማየሁ ጢሞቲዮስ ጉዳዩን በተመለከተ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ በተደረገው የተቀናጀ የፀጥታ ኦፕሬሽን በተጠርጣሪው ግለሰብ የተጠለፈች ወይዘሪት ፀጋ በላቸውን ማስጣል መቻሉን ተናግረዋል። ግንቦት 15 ቀን 2015 ዓ.ም ከመደበኛ ስራዋ ወጥታ ወደቤቷ ስታቀና ተጠርጣሪው ግለሰብ ከሌሎች ግብረ አበሮቹ ጋር የጠለፋ ወንጀል መፈጸሙን ገልጸዋል። ጉዳዩ ለፖሊስ ከደረሰ ጀምሮ ግብረ ሀይል በማቋቋም ወይዘሪት ፀጋ በላቸውን ከተጠርጣሪው ለማስመለጥና ወንጀለኞችን በቁጥጥር ስር ለማዋል የተቀናጀ ክትትል እና ጥረት ሲያደርግ መቆየቱን ተናግረዋል። ለዚሁ አጋዥ የሆነው በሀዋሳ ከተማ የተተከለው የደህንነት ካሜራ ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። ተጠርጣሪው ከነግብረ አበሮቹ ወደ ምስራቅ ጉጂ ቦሬ ከዚያም ጭሮ፣ ሻፋሞና አለታ ወንዶ ድረስ ወይዘሪት ጸጋን ይዞ አቅጣጫ ለማሳት በሚያደርገው ጥረት የጸጥታ ሀይሉ በልጅቱ ላይ ጉዳት ሳይደርስ በቁጥጥር ስር ለማዋል የተቀናጀ ስራ መስራቱን ተናግረዋል። ተጠርጣሪውና ግብረ አበሮቹን ለመያዝ የጸጥታ ሀይሉ ከአከባቢው ማህበረሰብ ጋር በመሆን በተደረገው ጥረት ማምለጥ አለመቻላቸውን ሲረዱ ወይዘሪት ፀጋ በላቸውን መልቀቃቸውን ነው ያብራሩት። እስከ አሁን ድረስ ፖሊስ ባደረገው ኦፕሬሽን ከጉዳዩ ጋር ግንኙነት የነበራቸውና የወንጀሉ ተጠርጣሪ የሆነ 11 ግለሰቦችን ፖሊስ በቁጥጥር ስር አውሎ ምርመራ መጀመሩን ተናግረዋል። አሁን ላይ ወይዘሪት ፀጋ በላቸው በመልካም ጤንነት ላይ እንደምትገኝ የገለጹት አቶ አለማየሁ በቀጣይ የማረጋጋትና የጤና ምርመራና ከተደረገላት በኃላ ፍትህ እንድታገኝ የክልሉ መንግስት አበክሮ ይሰራል ነው ያሉት። ወይዘሪት ፀጋ በላቸውን ከተጠርጣሪ ግለሰብ ለማስጣል በተደረገው ጥረት የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ የክልሉ የጸጥታ ሀይልና ሕዝቡ ላደረጉት ጥረት አመስግነዋል።