ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
በደቡብ ኢትዮጵያ የትምህርት ጥራት ስብራትን ለመፍታት የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው --- ቢሮው
Mar 19, 2024 49
አርባ ምንጭ ፤ መጋቢት 10/2016(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በትምህርት ዘርፍ የገጠመውን ስብራት ፈትቶ ለውጥ ለማምጣት የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ በትምህርት ተሃድሶ መርሃ-ግብር በተካሄደ የማህበረሰብ ንቅናቄ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ስድስት ወራት ከ420 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ መሰብሰቡ ተመላክቷል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ትምህርት ቢሮ ሃላፊና ማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ ዶክተር አበባየሁ ታደሰ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በክልሉ በትምህርት ዘርፍ የታየውን ስብራት ፈትቶ ለውጥ ለማምጣት እየተሰራ ነው። በክልሉ የትምህርት ጥራትን ከማስጠበቅ ጎን ለጎን ጥራት ያለው ፈተና በመስጠት ተማሪዎች በሀገርና በዓለም አቀፍ ደረጃ ብቁና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ሲሉም ገልጸዋል። አዲሱ ሥርአተ ትምህርት በሁሉም የትምህርት እርከኖች ተግባራዊ መደረጉን ጠቁመው፣ ከመዋዕለ ህፃናት ጀምሮ የትምህርት ግብአትን በማሟላት የትምህርት ጥራትና አግባብነትን ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የትምህርት ባለድርሻዎችንና ህዝብን በማሳተፍ በትምህርት ቤቶች ግንባታ፣ በማስፋፊያና በእድሳት ሥራዎች እንዲሁም በቁሳቁስ ማሟላት ጠንካራ ተግባራት መከናወናቸውንም ዶክተር አበባየሁ ተናግረዋል። በክልሉ በትምህርት ተሃድሶ መርሃ-ግብር በተካሄደ የማህበረሰብ ንቅናቄ በግማሽ ዓመቱ ከ420 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ መሰብሰቡንም አስረድተዋል። የትምህርት ቤቶችን መሠረተ ልማትና ግብአት በማሟላት የትምህርት ስብራትን በዘላቂነት ለመፍታት ባለድርሻ አካላትና ህዝቡ የጀመሩትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጥሪ አቅርበዋል። በክልሉ የባስኬቶ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ፍሬው ፍሻለው በበኩላቸው እንዳሉት፣ በዞኑ በትምህርት ዘርፍ ችግሮችን ፈትቶ ለውጥ ለማምጣት ማህበረሰቡን ያሳተፈ ሥራ እየተሰራ ነው። በዚህም የትምህርት ቤቶችን ደረጃ የማሻሻልና ትምህርት ቤቶችን ለተማሪዎች ምቹ ከማድረግ ባለፈ ለመምህራን አቅም ግንባታ ትኩረት መሰጠቱን ነው የገለጹት። የትምህርት ጥራት በመንግስት ጥረት ብቻ እንደማይረጋገጥ የገለጹት ዋና አስተዳዳሪው፣ "ባለድርሻ አካላትም የበኩላቸውን እንዲወጡ የሚያስችል አደረጃጀት ተፈጥሮ በቅንጅት እየተሠራ ነው" ብለዋል። ሁለንተናዊ ብልጽግና እንዲረጋገጥ በትምህርት ዘርፍ ለውጥ ለማምጣት የተጀመረው ሥራ መጠናከር እንዳለበት የገለጹት ደግሞ የክልሉ ምክር ቤት አባል ወይዘሮ ምስጋና ዋቀዮ ናቸው። በትምህርት ዘርፍ የሚሰራው ሥራ ለነገ መሰረት በመሆኑ የክልሉ ምክር ቤት አባላት በቁርጠኝነት የመደገፍና የመከታተል ሃላፊነታቸውን በመወጣት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። የመጻህፍት አቅርቦት፣ የመምህራን አቅም ግንባታ፣ የተማሪ መጻህፍና ክፍል ጥምርታ ማሻሻልን ጨምሮ ለትምህርት ዘርፍ ማነቆ የሆኑ ጉዳዮች እንዲፈቱ ከትምህርት ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሠራን ነው ብለዋል። የክልሉ ምክር ቤት በአርባ ምንጭ ከተማ ሰሞኑን ባካሄደው 2ኛ መደበኛ ጉባኤ ለትምህርት ጥራት መረጋገጥ አስፈጻሚ አካላትና የምክር ቤት አባላት ሚናቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ማስገንዘቡ የሚታወስ ነው።
ከፍተኛ የጸኃይ ጨረር በሰው ጤና ላይ ጉዳት ሊያደርስ ይችላል በሚል በማኅበራዊ ሚዲያው የሚሰራጨው መረጃ ኃሰተኛ ነው
Mar 18, 2024 212
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፡- በአዲስ አበባ ከፍተኛ የጸኃይ ጨረር በሰው ጤና ላይ ጉዳት ሊያደርስ ይችላል በሚል ማኅበራዊ ሚዲያው የሚሰራጨው መረጃ ሀሰተኛ መሆኑን የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ገለጸ። ሰሞኑን በማኅበራዊ ትስስር ገፆች በአዲስ አበባ በጤና ላይ ጉዳት ሊያደርስ የሚችል ከፍተኛ የፀኃይ ጨረር እንደሚኖር ተደጋጋሚ መረጃዎች እየወጡ ይገኛሉ። ይህን ተከትሎም አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ጉዳት ያደርስባቸዋል በሚል ከመማሪያ ክፍላቸው እንዳይወጡ ክልከላ ማድረጋቸውን ኢዜአ ከተለያዩ ምንጮች ማረጋገጥ ችሏል። አንዳንድ ወላጆችና የከተማዋ ነዋሪዎችም በዚሁ መረጃ ምክንያት መደናገር እንደተፈጠረባቸውም እንዲሁ። ጉዳዩን አስመልክቶ ኢዜአ የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት የስፔስና ፕላኔተሪ ሳይንስ ሥራ ክፍል መሪና ተመራማሪ ንጉሴ መዝገበ (ዶ/ር)ን አነጋግሯል። ባለሙያው፤ ከፍተኛ የጸኃይ ጨረር በሰው ጤና ላይ የከፋ ጉዳት ሊያደርስ ይችላል በሚል በማኅበራዊ ሚዲያ የተሰራጨው መረጃ ኃሰተኛና ከሳይንሱ ውጪ ነው ብለዋል። የጸኃይ ጨረር በሰዎች ጤና ላይ ሊያስከትል የሚችለው የጤና ጉዳት አለመኖሩንም አረጋግጠዋል። ያም ብቻ ሳይሆን ከጸኃይ የሚነሱ ሞገዶች ወይም ቅንጣቶች ወደ መሬት ወርደው ሰዎች ላይ ጉዳት የማድረስ አቅም የላቸውም ነው ያሉት። ይልቁንም ከጸኃይ የሚነሱ ጨረሮች በብዛት የሚያጠቁት ስፔስ ላይ ያሉ ሳተላይቶችን የመገናኛና የኮሙኑኬሽን መሣሪያዎችን መሆኑንም አብራርተዋል። አለም ዓቀፍ የስፔስ ትንበያዎች እንዲህ አይነት ጉዳት ሊያደርስ የሚችል ምንም አይነት ፍንጭ አለመስጠታቸውንና የተናፈሰው ሐሰተኛ መረጃ ምንጩ የማይታወቅ ነው ሲሉም ተናግረዋል። ኅብረተሰቡ የሚሰራጩ መረጃዎችን ትክክለኛነት ከሚመለከታቸው አካላት ማጣራት እንዳለበት ገልጸው፣ የእለት ተእለት እንቅስቃሴውን ያለምንም ሥጋት ሊቀጥል ይገባልም ብለዋል።
በኦሮሚያ ክልል የወባ በሽታን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የተሰሩ ስራዎች ውጤት አስገኝተዋል - የክልሉ ጤና ቢሮ
Mar 18, 2024 94
ጅማ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የወባ በሽታን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የተሰሩ ስራዎች ውጤት ማስገኘታቸውን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የ2016 በጀት ዓመት የመጀመሪያው አጋማሽ የወባና የቲቢ በሽታን ጨምሮ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች መከላከልና ቁጥጥር ስራዎች አፈጻጸም ግምገማ ዛሬ በጅማ ማካሄድ ጀምሯል። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ደረጀ አብደና በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት ቢሮው በተለያዩ ምክንያቶች የጨመረውን የወባ በሽታ ለመከላከል ሕዝብን ያሳተፈ ተግባራትን አከናውኗል። በዚህም ከሰባት ሚሊዮን በላይ የአልጋ አጎበር ስርጭትና የኬሚካል ርጭት የተካሄደ ሰሆን፣ ኅብረተሰቡም በየአካባቢው ለወባ መራቢያ የሆኑ ቦታዎችን አጽድቷል ብለዋል። በክልሉ በሚገኙ የጤና ተቋማት ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ ምርመራ ካካሄዱ 3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሰዎች ውስጥ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን የሚሆኑት በወባ መያዛቸውን ገልጸዋል። በክልሉ ባለፉት ሶስት ዓመታት ይከሰት የነበረው የወባ በሽታ መጠን በዓመት ከ200 ሺህ የማይበልጥ እንደነበር ጠቁመዋል። የወባ በሽታን ለመከላከል የአካባቢን ጽዳት መጠበቅ፣ያቆረ ውሃን ማስወገድና አጎበርን በአግባቡ መጠቀም እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል። ኅብረተሰቡ የበሽታው ምልክቶች ሲታይበት ፈጥኖ ወደ ጤና ተቋማት በመሄድ ሕክምናውን እንዲከታተልም ምክትል ቢሮ ኃላፊው አሳስበዋል። በአጠቃላይ ባለፉት ስድስት ወራት የወባ በሽታን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የተሰሩ ስራዎች ውጤት ማስገኘታቸውን አስረድተዋል። የጅማ ዞን ጤና ጽህፈት ኃላፊ አቶ ፉአድ ሳሲት፣ በዞኑ በስምንት ወረዳዎች በበሽታው የተያዙ ከ26ሺህ በላይ ሰዎች ህክምና እንደተደረገላቸው ገልጸዋል። በኦሮሚያ ክልል የሰሜን ሸዋ ዞን ጤና ጽህፈት ቤት የወባ መከላከል ኦፊሰር ሲስተር ምስራቅ ዘነበ፣ በበኩላቸው በዞኑ የወባ በሽታ ለመከላከል እየተሰራ ቢሆንም፤ የመድኃኒትና የህክምና መሳሪያዎች እጥረት እንደገጠማቸው ተናግረዋል። ኅብረተሰቡ ራሱን ከወባ በሽታ መከላከል እንዲችል የግንዛቤ ማስረጽ ሥራ በስፋት መካሄዱን አስታውቀዋል። የበሽታው ምልክት የታየባቸው ሰዎች በፍጥነት ህክምና እንዲያገኙ መደረጉን ሲስተር ምስራቅ ገልጸዋል።
በአዲስ አበባ በ16 ተቋማት ላይ የተካሄደው ሪፎርም ተግባራዊ መደረግ ጀመረ
Mar 18, 2024 86
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ በ16 ተቋማት ላይ የተካሄደው የሠራተኞች ምዘናና ምደባ የሪፎርም ሥራ ተጠናቆ ወደ ትግበራ ምዕራፍ መግባቱን የከተማዋ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ኃብት ልማት ቢሮ ገለጸ። የቢሮው ኃላፊ ጣሰው ገብሬ(ዶ/ር)፤ በከተማዋ የሚሰጠውን አገልግሎት ለማሻሻል በተያዘው በጀት ዓመት በ16 ተቋማት ሪፎርም መደረጉን ጠቁመዋል። ሪፎርሙን ተከትሎ የአሠራር ሥርዓት ማሻሻያ ከማዕከል እስከ ወረዳ አደረጃጀት መሠራቱን ገልፀዋል። በቴክኖሎጂ የሚደገፍ አገልግሎት የመለየት ሥራ መሠራቱን አንስተው፤ የሠራተኛ ብቃት ምዘና መደረጉንም አስረድተዋል። የብቃት ምዘናውን ከ19 ሺህ በላይ የሆኑ ሠራተኞች መውሰዳቸውን ጠቅሰዋል። ከተፈታኞቹ መካከል 33 ነጥብ 3 በመቶ አመራሮች እንዲሁም 50 ነጥብ 6 በመቶው ሠራተኞች ማለፋቸውን ተናግረዋል። ምዘናውን ያለፉ 99 በመቶ ኃላፊዎች እንዲሁም 88 በመቶ የቡድን መሪና ሠራተኞች መመደባቸውን አስረድተዋል። ፈተናውን ያላለፉትም በድልድል ደንቡ መሠረት ሁለት ደረጃ ዝቅ ብለው መመደባቸውን ገልፀዋል። ምዘናውን ተከትሎ ከ17 ሺህ በላይ ሠራተኞች በሁለት ዙር የአቅም ግንባታ ሥልጠና መውሰዳቸውንም ተናግረዋል። ሪፎርሙ የዝግጅት ምዕራፍ ተጠናቆ ከዛሬ ጀምሮ ወደ ትግበራ መገባቱን ነው ቢሮ ኃላፊው የገለፁት።
በዘንድሮ ዓመት የ12ኛ ክፍል አገር አቀፍ ፈተናን ለመውሰድ ከ670 ሺህ በላይ ተማሪዎች ተመዝግበዋል
Mar 18, 2024 126
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦በዘንድሮ ዓመት የ12ኛ ክፍል አገር አቀፍ ፈተናን ለመውሰድ ከ670 ሺህ በላይ የተማሪዎች ምዝገባ መካሄዱን የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት ገለጸ። የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር እሸቱ ከበደ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለዘንድሮው አገር አቀፍ የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና የተሳካ ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ ነው። ይህንንም ተከትሎ ተማሪዎች የሚፈተኗቸውን የትምህርት ዓይነቶች አውቀው ዝግጅት እንዲያደርጉ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር መከናወኑን አንስተዋል። ተማሪዎች በሥነ-ልቦና እራሳቸውን እንዲያዘጋጁ የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውንም ጠቅሰዋል። ለአገር አቀፉ የ12ኛ ክፍል ፈተና የሚቀመጡ የተፈታኝ ተማሪዎች ምዝገባ ከየካቲት 3 እስከ የካቲት 30/2016 ዓ.ም እንደሚያከናውን ተቋሙ መግለጹ ይታወሳል። ይህንንም ተከትሎ ተቋሙ የፀጥታ ችግር ካለባቸው አንዳንድ አካባቢዎች በስተቀር በአብዛኛው አገሪቱ አካባቢዎች የተማሪዎች ምዝገባ ተካሂዶ መጠናቀቁን ጠቁመዋል። በዚህም እስካሁን ከ670 ሺህ በላይ ተማሪዎች ፈተናውን ለመውሰድ መመዝገባቸውን ገልፀዋል። የተቀሩት የፀጥታ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች የሚገኙ ተፈታኝ ተማሪዎች ምዝገባ ደግሞ በዚህ ሣምንት እንደሚከናወን ነው ያረጋገጡት። የፈተና ዝግጅት ሥራው የአገሪቱን ሥርዓተ ትምህርት የተከተለና ተማሪዎቹን በአግባቡ ለመመዘን በሚያስችል መልኩ መዘጋጀቱን ጠቅሰዋል። የፈተናው ዝግጅት እየተገባደደ መሆኑን አንስተው በቀጣይ የፈተናው ሕትመት እንደሚጀመር ገልፀዋል። የዘንድሮ የ12ኛ ክፍል አገር አቀፍ መልቀቂያ ፈተና የመስጫ ሰሌዳ ወደፊት ይፋ ይሆናል ተብሏል።
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የቆጣሪ ውል እድሳቱን እስከ ሰኔ 30/2016 ዓ.ም አራዘመ
Mar 18, 2024 87
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ለቀጣይ አምስት ዓመታት የሚያገለግል የቆጣሪ ውል የእድሳት ጊዜ እስከ ሰኔ 30/2016 ዓ.ም ማራዘሙን ገለጸ። ተቋሙ የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ተጠያቂነትን ለማስፈን ያስችላል ያለውን ይኸው የውል እድሳት ከሕዳር 1 እስከ መጋቢት 30/2016 ዓ.ም ነበር ለማከናወን አቅዶ ወደ ሥራ የገባው። ይሁንና በተለያዩ ምክንያቶች የቆጣሪ ውል እድሳቱን እስከ ሰኔ 30/2016 ዓ.ም መራዘም ማስፈለጉን ነው የተቋሙ የኮርፖሬት የኮሙኑኬሽን ዳይሬክተር መላኩ ታዩ ለኢዜአ የገለጹት። የውል እድሳቱ ቆጣሪ ከወሰዱ ከአምስት ዓመታት በላይ የሆናቸውን ደንበኞችን ብቻ የሚመለከት መሆኑን ተናግረው እድሳቱ ምንም አይነት ክፍያ እንደማይጠይቅ ጠቁመዋል። በመሆኑም ደንበኞች በአቅራቢያቸው ባሉ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ማዕከል በመሄድ በተሰጠው የጊዜ ገደብ የውል እድሳቱን እንዲያከናውኑ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። ከሕዳር 1/2016 ጀምሮ ከ21 ሺ በላይ ደንበኞች የውል እድሳት ማድረጋቸውን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ገልጿል። የውል እድሳቱ ቆጣሪን ለማይታወቅ አካል የሚያስተላልፉ ደንበኞችን ለመቆጣጠር፣ የኃይል ሥርቆትን ለማስቀረት እንዲሁም የኃይል መቆራረጥ ችግር ለማቃለል እንደሚያስችል ተገልጿል።
በሆሮጉድሩ ወለጋ የዓመታት ጥያቄ የነበሩ መሰረተ ልማቶች አገልግሎት መስጠት ጀመሩ
Mar 18, 2024 88
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ ክፍለ ጦሩ በሆሮ ጉድሩ ወለጋ በሀባቦ ጉድሩ ወረዳ ከገባ ጊዜ ጀምሮ በሽብር ቡድኑ ላይ እየወሰደ ባለው እርምጃ የአካባቢውን ሰላም ከመመለስ ባሻገር ለበርካታ አመታት አገልግሎት ሳይሰጡ የቆዩ የንፁህ መጠጥ ውሀ እና የኔትወርክ አገልግሎት ስራ ጀምረዋል። በስፍራው ተገኝተው አገልግሎትን ያስጀመሩት የክፍለ ጦሩ አዛዥ ሌተናል ኮሎኔል ገዛኸኝ በቀለ ህብረተሰቡ ውይይቶች ላይ በተደጋጋሚ ሲያነሳቸው የነበሩ የንፁህ መጠጥ ውሀ እንዲሁም የኔትወርክ ጥያቄዎች የተመለሱ ሲሆን ቀጣይ ከወረዳ አስተዳደሮች ጋር በጋራ በመስራት ሌሎች የህብረተሰቡ ጥያቄዎች ይመለሳሉ ብለዋል። የሀባቦ ጉድሩ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ከበደ ጉርሜሳ የሰራዊቱን ጀግንነትና ቁርጠኝነት አድንቀው በወረዳው ውስጥ በሽብር ቡድኑ ቁጥጥር ስር የነበሩ ቀበሌዎች ሰራዊቱ በወሰደው እርምጃ ነፃ የወጡ ሲሆን በተፈጠረው ሰላም የህብረተሰቡን ጥያቄዎች መመለስ ጀምረናል ሲሉ ገልፀዋል። የቃዎ ቀበሌ ነዋሪዎች የንፁህ መጠጥ ውሀ እና የኔትወርክ አገልግሎት መሥጠት መጀመሩን አመስግነው የመጠጥ ውሀ ለማግኘት ከአንድ ሰዓት ተኩል በላይ የእግር ጉዞ ይጓዙ እንደነበር መናገራቸውን ከመከላከያ ሰራዊት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
በኢትዮጵያ ዘላቂ ሠላም እንዲረጋገጥ ለንግግርና ሠላማዊ አማራጮች ቅድሚያ መስጠት ይገባል -ካውንስሉ
Mar 17, 2024 287
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ዘላቂ ሠላም እንዲረጋገጥ ለንግግርና ሠላማዊ አማራጮች ቅድሚያ መስጠት እንደሚገባ የኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል አመለከተ። ካውንስሉ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ የጸሎት፣ምስጋናና ምልጃ መርሃ ግብር አካሂዷል። በመርሃ ግብሩ ላይ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ አማኞች፣ ከተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት የተወጣጡ የኃይማኖት አባቶችና ዘማሪያን ተሳትፈዋል። በኢትዮጵያ ሠላም፣ ዕድገትና አንድነት እንዲመጣ እንዲሁም ከፈጣሪ ጋር እርቅ እንዲወርድ በኃይማኖት አባቶች ጸሎት የተደረገ ሲሆን ህጻናትም መንፈሳዊ መዝሙሮችን አቅርበዋል። የኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል ፕሬዝዳንት ዶክተር ጣሰው ገብሬ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ መርሃ ግብሩ የተዘጋጀው በኢትዮጵያ ፍቅር፣ አንድነትና ሠላም እንዲመጣ ወደ ፈጣሪ በህብረት ለመማለድ ነው። በኢትዮጵያ ዘላቂ ሠላም እንዲመጣ ለሠላማዊ አማራጮችና ለንግግር ጊዜና ቦታ መስጠት እንደሚገባ በማሳሰብ ሁሉም ወገኖች ለሠላማዊ አማራጮች ቅድሚያ ሊሰጡ ይገባል ብለዋል። የኢትዮጵያ ወንጌላዊያን አብያተ ክርስቲያናት ህብረት ፕሬዝዳንት ፓስተር ጻድቁ አብዶ በበኩላቸው በኢትዮጵያ አንድነትና ሠላም እንዲረጋገጥ እርስ በርስ መከባበርና የሌላውን ስሜትና ህመም መረዳት ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። የእምነቱ ተከታዮች የእምነቱ አስተምህሮ በሚያዘው መሰረት የሚጠበቅባቸውን ሚና መወጣት እንዳለባቸው አጽንኦት ሰጥተዋል። የዘጸአት አፖስቶሊክ ሪፎርሜሽን ቤተ ክርስቲያን መሥራችና ዋና መጋቢ ሃዋሪያ ዮሃንስ ግርማ ሁላችንም ለሰላም መረጋገጥ በጋራ ልንሰራ ይገባል ብለዋል፡፡ ለሰላም መስፈን ከህዝቡ ብዙ ይጠበቃል ያሉት ዋና መጋቢ ሃዋርያ ዮሃንስ ዕድገት የሚረጋገጠው ሠላም ሲረጋገጥ በመሆኑ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ጠይቀዋል።
አለመግባባቶች በዘላቂነት እንዲፈቱ ወደ ፈጣሪ መጸለይ ይገባል - የኢትዮጵያ ወንጌላዊያን አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል ፕሬዝዳንት
Mar 17, 2024 232
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦ ልዩነቶች እና አለመግባባቶች በዘላቂነት እንዲፈቱ ወደ ፈጣሪ መጸለይ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ወንጌላዊያን አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል ፕሬዝዳንት ዶክተር ጣሰው ገብሬ ተናግረዋል፡፡ ፕሬዝዳንቱ የንስሐ፣ የምልጃ እና የምስጋና መርሐ -ግብሩ በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን እንዲሁም ወደ ኋላ የማይመለስ እርቅ እንዲፈጠር የወንጌል አማኞች የሚጸልዩበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አክለውም መርሐ -ግብሩ ምዕመኑ ለሀገሪቱ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲያደርግ "ጌታ እንዲረዳው" የሚማልድበት መሆኑን ማስታወቃቸውን ኢቢሲ ዘግቧል፡፡ በመርሃ ግብሩ ላይ በኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል ስር ያሉ የተለያዩ ቤተክርስቲያናት መሪዎች፣ አባቶች፣ ዘማሪያን፣ መጋቢዎች እና ሌሎችም ተገኝተዋል።
የሙስና መከላከል ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራትን በዕውቀትና በክህሎት ለመከወን ጥረት እየተደረገ ነው
Mar 17, 2024 202
አዳማ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦ ህብረተሰቡን እያማረሩ ያሉ የሙስና ወንጀሎችን ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራትን በዕውቀትና በክህሎት በማስደገፍ ለመከወን ጥረት እየተደረገ መሆኑን የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ገለፀ ። ከሁሉም የፌዴራል ተቋማትና የልማት ድርጅቶች የተወጣጡ ከ900 በላይ የሚሆኑ የስነ ምግባር መኮንኖችና ሃላፊዎች የተሳተፉበት የሙስና መከላከል አቅም ግንባታና ክህሎት ስልጠና በአዳማ አባገዳ አዳራሽ ተጀምሯል ። በፌዴራል ስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን የስልጠናና አቅም ግንባታ ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር አቶ ወዶ አጦ በተለይ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ የሙስና መከላከል ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ተግባሩን በዕውቀትና ክህሎት ለማስደገፍ እየተሰራ ነው። ለዚህም መድረኩ ሁሉም የስነ ምግባር መኮንኖችና ሃላፊዎች በመግባባት የጋራ አረዳድና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ወጥ የሆነ ግንዛቤ እንዲይዙ፣ የሙስና መከላከልና ተጋላጭነትን በመቀነስ ረገድ ተጨማሪ አቅም እንዲፈጥሩ ለማስቻል ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። በፌዴራል ደረጃ 25 የትኩረት ዘርፎች መለየታቸውን ጠቅሰው በ22ቱ ዘርፎች ላይ የሙስና መከላከል ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የዕውቀት፣የክህሎትና የአቅም ግንባታ ስራዎች መሰራታቸውን ገልፀዋል። የሙስና ተጋላጭነት ደረጃን ለማወቅና የተቀናጀ የመከላከል ስራ ለማከናወን ከተለዩት 25 ዘርፎች 19 በሚሆኑት ላይ ጥናቶች በማካሄድ ረገድ የተሳካ ስራ መሰራቱን ገልፀው በቀሪዎቹ ስድስት ዘርፎች ላይም ጥናቶች እየተከናወኑ መሆናቸውን አስረድተዋል። በየተቋማቱ ያለው የሙስና ተጋላጭነት መንስኤ ብልሹ አሰራር የአመራሩና የሰራተኛው የስነ ምግባር ጉድለት መሆኑን የገለፁት ምክትል ኮሚሽነሩ ችግሮቹን ለመቅረፍ በጥናት የተደገፉ ስራዎች እየተሰሩ እንደሆነም ገልፀዋል። በ19 ዘርፎች የተካሄደውን የሙስና ተጋላጭነት የጥናት ግኝት ውጤት ተቋማቱ በዕቅዳቸው አካተው እንዲሰሩበት ግብረመልስ መሰጠቱን ተናግረዋል ። በአሁኑ ወቅት ህብረተሰቡን እያማረረ ያለው በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚፈፀም የሙስና ወንጀል አንዱ መሆኑን ያነሱት ደግሞ በኮሚሽኑ የሙስና መከላከል ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር አቶ እሸቴ አስፋው ናቸው። በየደረጃው ባሉ ተቋማትና የልማት ድርጅቶች የሚፈፀሙ የሙስና ወንጀሎችን በመዋጋት ረገድ የመላው የስነ ምግባር መኮንኖችና የስራ ሃላፊዎች ሚና የጎላ መሆኑን ገልፀዋል። ''በጥናትና በዕውቀት ላይ የተመሰረተ የሙስና መከላከል ስራን ለማከናወን የክህሎትና የስነ ምግባር ጉድለቶችን የሚቀርፍ አቅምን መፍጠር አለብን'' ብለዋል። በተጨማሪም ጠንካራ የሙስና መከላከል ተደራሽነትን እውን ለማድረግ ውጤት ተኮር ተግባራት ላይ በማተኮር እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው የስነ ምግባር መኮንኖችና የስራ ሃላፊዎች ከስልጠናው ጎን ለጎን የምዘና ፈተና እንደሚወስዱም አቶ እሸቴ ተናግረዋል።
ለሀገር ሰላምና አንድነት የጸሎትና ምስጋና መርሃ ግብር እየተካሄደ ነው
Mar 17, 2024 182
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦ ለሀገር ሰላምና አንድነት የጸሎትና ምስጋና መርሃ ግብር በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ እየተካሄደ ነው። የጸሎትና ምስጋና መርሃ ግብሩ በኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ቤተ ክርስቲያናት ካውንስል የተዘጋጀ ነው። በዚህም መሰረት በርካታ የእምነቱ ተከታዮች የታደሙበት የጸሎትና ምስጋና መርሃ ግብር በመስቀል አደባባይ በመካሄድ ላይ ይገኛል። የጸሎትና ምስጋና ስነ ስርአቱ በተለይም ስለ ሰው ልጆች ሁሉ ሰላም፤ የሀገር ሰላምና አንድነትን በተመለከተ በፀሎትና ዝማሬ ለፈጣሪ ምስጋና የሚቀርብበት ነው። በመርሃ ግብሩ ላይ በኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ቤተ ክርስቲያናት ካውንስል ስር ያሉ የተለያዩ ቤተክርስቲያናት መሪዎች፣ አባቶች፣ ዘማሪያን፣ መጋቢዎች እና ሌሎችም ተገኝተዋል።
በከፍተኛ ትምህርት ላይ እየተተገበሩ ያሉ የለውጥ ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ የዘርፉ ሃላፊዎች በትኩረት መስራት አለባቸው- የትምህርት ሚኒስቴር
Mar 17, 2024 76
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦ በከፍተኛ ትምህርት ላይ እየተተገበሩ ያሉ የለውጥ ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ የዘርፉ ሃላፊዎች በትኩረት መስራት እንደሚገባቸው የትምህርት ሚኒስቴር አሳሰበ፡፡ “ከፍተኛ ትምህርት ከፍ ላለ ተጽዕኖ” በሚል መሪ ቃል የተካሄደው የከፍተኛ ትምህርት ፕሬዝዳንቶች ፎረም ተጠናቋል፡፡ በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ኮራ ጡሽኔ በማጠቃለያው ላይ እንዳሉት ከፍተኛ ትምህርት ላይ እየተተገበሩ ያሉት ቁልፍ የለውጥ ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ የዘርፉ ሃላፊዎች ትልቅ አላፊነት አለባቸው ። ሃላፊዎቹ እየተተገበሩ ያሉት ቁልፍ የለውጥ ስራዎችን በትኩረት በመስራት የድርሻቸውን መወጣት እንደሚገባቸውም አሳስበዋል፡፡ ቁልፍ የለውጥ ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ የሁሉንም ባለድርሻዎች የላቀ ተሳትፎ እንደሚጠይቅ አስታውቀዋል። ፎረሙ በተጀመሩ የለውጥ መርሃ-ግብሮች አተገባበር፣ የለውጥ ስኬቶችና ባጋጠሙ ተግዳሮቶች ዙሪያ ጥልቅ ውይይት ማድረጉ ተገልጿል። ለተከታታይ ሁለት ቀናት የቆየው ፎረም የቀጣይ ስራ አቅጣጫዎች ላይ በመምከር ነው የተጠናቀቀው፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱን ጨምሮ ከመላው የሀገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች የተውጣጡ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶችና የስራ ሃላፊዎችን ጨምሮ ሌሎች ባለድርሻ አካላት በፎረም ላይ ተሳትፈዋል፡፡
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በትምህርት ዘርፍ የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት ይጠናከራል
Mar 17, 2024 113
ቦንጋ ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በትምህርት ዘርፍ የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት እንደሚጠናከር የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጅነር ነጋሽ ዋጌሾ ገለፁ። የ2ኛ ደረጃ ተማሪዎችን የትምህርት ተሳትፎና ውጤት ማሻሻል ላይ ያተኮረ ክልላዊ የውይይት መድረክ በቦንጋ ከተማ ተካሄዷል። በመድረኩ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳደር ዶክተር ኢንጅነር ነጋሽ ዋጌሾ፣ በክልሉ በትምህርት ዘርፍ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የተቀናጀ ጥረት ይጠናከራል ብለዋል። "በትምህርቱ ዘርፍ ከገጠመን ውድቀት ለመውጣት በተግባር የተደገፈ ቁርጠኝነት ከሁላችንም ያስፈልጋል" ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ለተማሪዎች በቂ ድጋፍ በማድረግ በእውቀትና በስነልቦና ብቁና ዝግጁ እንዲሆኑ እንደሚሰራ ተናግረዋል። በዚህም መምህራን፣ ሱፐርቫይዘሮችና ርዕሳነ መምህራን የትምህርት ጥራትንና የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ለማሻሻል በሚደረገው ርብርብ ውስጥ ግንባር ቀደም ተሳትፎአቸውን ማጠናከር ይገባቸዋል ብለዋል። የመምህራን ጥቅማጥቅም ካለመከበር፣ ደመወዝ በወቅቱ ካለመከፈልና ከሌሎች ጉዳዮች ጋር በተያያዘ የሚስተዋሉ ችግሮች በትምህርት ጥራትና ውጤት ላይ ተፅእኖ ስለሚያሳድሩ ክልሉ ችግሩን ለመቅረፍ ቅድሚያ ሰጥቶ ይሰራል ብለዋል። ''መምህራን የተሰጣቸው የዜግነት ግዴታ ትልቅ በመሆኑ ችግር ሳይበግራቸው ያስተማሯቸው ተማሪዎች በሀገር አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ውጤታማ እንዲሆኑ መትጋት አለባቸው'' ብለዋል። ተቋርጦ የቆየውን የክረምት ትምህርትና ስልጠና መርሃ ግብር በማስቀጠል የመምህራንን አቅም ለማጎልበትና ተጠቃሚነታቸውን ለማሻሻል እንደሚሰራም ተናግረዋል። የመምህራንና የትምህርት አመራሮች ቁርጠኝነት ለተማሪዎች ውጤት መሻሻል የጎላ ሚና እንዳለው የገለፁት ደግሞ የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አልማው ዘውዴ ናቸው። በትምህርቱ ዘርፍ ብዙ ጉድለቶች ቢኖሩም ያለንን አቅም በሙሉ ተጠቅመን ዘርፉን ለመታደግ በቁርጠኝነት እና በኃላፊነት ስሜት እንሰራለን ብለዋል። በክልሉ ከሚገኙ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በመቀናጀት ትምህርት ቤቶችን የመደገፍና ተማሪዎችን የማብቃት እንዲሁም ደረጃ የማሻሻልና ሌሎች ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደም ለትምህርት ተደራሽነት የተሰጠው ትኩረት ለጥራቱ አለመሰጠቱ አሁን ላለንበት ውጤት አብቅቶናል ያሉት ከመድረኩ ተሳታፊዎች የሸካ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር አቶ አምባዬ ማሞ ናቸው ። ካለፈው ወድቀት በመማር ዘንድሮ የ12ኛ ክፍልን ውጤት ለማሻሻል ተማሪዎችን የመደገፍና በስነልቦና ማብቃት ላይ ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ መሆናቸውንም ተናግረዋል። የሺሺንዳ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ሱፐርቫይዘር ታፈሰ ማሞ በበኩላቸው፣ የተማሪዎችን ውጤት ለማሻሻል ከማህበረሰቡና ከመምህራን ጋር በመወያየት የጋራ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ማሻሻል ለተማሪዎች ውጤት ማደግ ወሳኝ በመሆኑ ህብረተሰቡን በማስተባበር የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። በውይይት መድረኩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
የአገሪቱን የዕደ-ጥበብና የኪነ-ጥበብ ሀብቶች ተንከባክቦ ለመጠበቅ ጥረት እየተደረገ ነው
Mar 16, 2024 152
አርባ ምንጭ፤ መጋቢት 7 / 2016 (ኢዜአ)፡- የአገሪቱ የዕደ-ጥበብና የኪነ-ጥበብ ሀብቶች ተንከባክቦና ጠብቆ ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ገለጸ። የፌዴራልና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የስራ ሃላፊዎች ዛሬ በጋሞ ዞን የሚገኙ የዕደ-ጥበብና የኪነ-ጥበብ ሀብቶችን በመጎብኘት አበረታተዋል። በዚህ ወቅት የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የኪነ-ጥበብ፣የስነ-ጥበብና የፈጠራ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ነፊሳ አልማሃዲ እንዳሉት፤ የጉብኝቱ ዓላማ ዘርፉ ለሀገር ኢኮኖሚና ገጽታ ግንባታ ያለው ድርሻ እንዲጠናከር ለመደገፍ ነው። ሚኒስቴሩ የኪነ-ጥበብ፣የስነ-ጥበብና የፈጠራ ሥራዎችን በማስተዋወቅ፣የቴክኖሎጂ ሽግግርና የገበያ ትስስር በመፍጠሩ ረገድ አበክሮ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል። የአገራችን የኪነ-ጥበብና የስነ-ጥበብ ሀብቶች የጎብኚዎችን ቀልብ በመሳብ እያበረከተ ያለውን ሚና ለማጠናከር የመስሪያ ዕቃዎች እንዲዘምኑ ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በቅንጅት እየሠራን ይገኛል ብለዋል። ዕደ-ጥበብና የኪነ-ጥበብ ሀብቶች ለሀገር ኢኮኖሚ ትልቅ ድርሻ እንዳላቸው ጠቅሰው፤ ዘርፉን በቴክኖሎጂ ሽግግርና በግብአት አቅርቦት ለማጠናከር ባለሀብቶች መሳተፍ እንዳለባቸው አመልክተዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማህበራዊ ልማትና ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ ወርቀሰሙ ማሞ በበኩላቸው በጉብኝታቸው በአርባ ምንጭና ጨንቻ አካባቢ የሚገኙ የዕደ-ጥበብና የኪነ-ጥበብ እንቅስቃሴን ከተመለከቷቸው መካከል እንደሚገኙበት ተናግረዋል። በዚህም በዘርፉ የተሰማሩ አካላት ተጠናክረው ይበልጥ ተወዳዳሪ ለመሆን እንዲተጉ መነቃቃት እንዲፈጠር መደረጉን ገልጸዋል። በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን በመፍታት በአገርና በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ በባህልና ስፖርት ሚኒስቴር እየተደረገ ያለው አበረታች ጥረት በማጠናከር ዘርፉ ለሀገር ኢኮኖሚና ገጽታ ግንባታ ያለውን ድርሻ ለማሳደግ ይሰራልም ብለዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ለሀገር ኢኮኖሚ ትልቅ ድርሻ ያለው ሰፊ የዕደ-ጥበብ፣የኪነ-ጥበብና የፈጠራ ሀብቶች መኖራቸውን የተናገሩት ደግሞ የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ሃላፊ ወይዘሪት ፍሬህይወት ዱባለ ናቸው። የዕደ-ጥበብና የኪነ-ጥበብ ኢንዱስትሪው የአገሪቱን ብልጽግና ለማረጋገጥ እንደሚያግዝ ያመለከቱት ሃላፊዋ ይህን ሀብት ለመጠቀም በልዩ ትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በዘርፉ የተሰማሩ ወገኖችን በማደራጀትና በመደገፍ ብሎም የገበያ ትስስር በመፍጠሩ ረገድ ቢሮው የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል። የስራ ሃላፊዎቹ በአርባ ምንጭ የጃኖ እና የሸማ ፓርኮች እንዲሁም በጨንቻ የዶርዜ መንደር እና የማረሚያ ተቋም ዕደ-ጥበብና የኪነ-ጥበብ ሥራዎችን ጎብኝተዋል።
ሀገራዊ የምክክር ሂደቱ ወደ አጀንዳ ማሰባሰብ ምዕራፍ እየገባ ነው - ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ
Mar 16, 2024 150
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ ለብሔራዊ መግባባትና ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ ታላቅ መሠረት የሚሆነው ሀገራዊ የምክክር ሂደት ወደ አጀንዳ ማሰባሰብ ምዕራፍ እየገባ መሆኑን የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የአጀንዳ ማሰባሰብና የሀገራዊ ጉባኤ ተሳታፊዎች አሰራር ስርዓት የግብዓት ማሰባሰቢያ የውይይት መድረክ አካሂዷል፡፡ የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ በዚሁ ጊዜ ባደረጉት ንግግር፤ የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት የሀገራዊ ምክክሩ ወሳኝ ምዕራፍ ነው ብለዋል፡፡ ሀገራዊ ምክክሩ መግባባት ላይ ባልተደረሰባቸው ቁልፍ ጉዳዮች መግባባት ላይ እንዲደረስ የሚያስችል በመሆኑ፥ ኢትዮጵያውያን ተወያይተው የጋራ መፍትሔ እንዲያስቀምጡ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ሀገራዊ ምክክር ለሀገረ-መንግሥት ግንባታ ትልቅ መሠረት የሚጥል ነው ያሉት ፕሮፌሰር መስፍን፤ አሁን ላይ ወደ አጀንዳ ማሰባበስብ ምዕራፍ እየተገባ መሆኑንም ተናግረዋል። ኮሚሽኑ ከዚህ ቀደም ለምክክሩ ወሳኝ እና ተከታታይ የሆኑ ሥራዎችን ሲሰራ መቆየቱን ገልጸው፤ ለዚህም በርካታ ተባባሪ አካላት መሳተፋቸውን ገልጸዋል። በአጀንዳ አሰባሰብ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ላይ የተገኙት ባለድርሻ አካላት በበኩላቸው፥ ኮሚሽኑ በምክክር ሂደቱ ላይ ሁሉም ህብረተሰብ ተሳታፊ እንዲሆን እየሰራ መሆኑን መገንዘባቸውን አንስተዋል። በመሆኑም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች በህብረታቸው አማካኝነት በምክክር ሊሳተፉ እንደሚገባ ጠቁመዋል። የፖለቲካ ፓርቲዎች በፌዴራል ደረጃ ለሚካሄዱ የአጀንዳ ማሰባሰብ ስራዎች ተወካዮችን ቀድመው እንዲያዘጋጁ ከወዲሁ ማሳወቅ እንደሚገባም ነው ሀሳባቸውን የሰነዘሩት። ለተነሱት አስተያየቶችና ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነሮች፥ በምክክሩ ሂደት ሁሉም ኢትዮጵያውያን እንደሚሳተፉ አረጋግጠዋል፡፡ የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽነር አምባዬ ኡጋቶ፥ በኮሚሽኑ የአሰራር ሂደት የሁሉም ኢትዮጵያዊ አቋም እና አጀንዳ እንደሚስተናገድ መግባባት ላይ ተደርሶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል፡፡ ከምክክር ሂደቱ የሚገለል አንድም አካል የለም ያሉት ኮሚሽነሩ፥ ኮሚሽኑ ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ በህግ የተሰጠውን ሃላፊነት እየተወጣ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ኮሚሽኑ የተሳታፊ ልየታ ባካሄደባቸው ሁሉም ወረዳዎች አካል ጉዳተኞች እንዲካተቱ መደረጋቸውን የገለጹት ደግሞ ኮሚሽነር ብሌን ገብረመድህን ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ በሰጡት ምላሽ፥ በምክክር ሂደቱ የከፍተኛ ትምህርት ተማሪዎችን ጨምሮ ሁሉም ይሳተፋሉ ብለዋል፡፡ ኮሚሽኑ ዛሬ ባካሄደው የአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት የአሰራር ስርዓት ውይይት ላይ የተገኙ ተሞክሮዎችን እና ሃሳቦችን በመቀመር ለሂደቱ ስኬታማነት ጥቅም ላይ እንደሚያውላቸውም አንስተዋል። በቀጣይም ከሌሎች ባለደርሻ አካላት ጋር የተለያዩ ውይይቶች እንደሚካሄዱ ጠቁመዋል፡፡ በተካሄደው የውይይት መድረክ ሚኒስትሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች፣ ከሁሉም ክልሎች የተወከሉ ባለድርሻ አካላት እና የሲቪል ማኅበረሰብ ተወካዮችን ጨምሮ ሌሎችም ተሳትፈዋል።
በዛሬው እለት በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች የዓድዋ ድል መታሰቢያን ጎብኝተዋል
Mar 16, 2024 162
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦በዛሬው እለት በሺዎች የሚቆጠሩ የህብረተሰብ ክፍሎች የዓድዋ ድል መታሰቢያን መጎብኘታቸው ተገለጸ። መታሰቢያው ከዛሬ ጀምሮ ለህዝብ እይታ ክፍት መሆኑን ተከትሎ በሺዎች የሚቆጠሩ የመዲናዋ ነዋሪዎች፣ ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ ዜጎች፤ የአንደኛና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች እንዲሁም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ጉብኝት አካሂደዋል፡፡ ዲያስፖራዎች፣ የውጭ ሀገራት ዜጎች እና ከተለያየ የህብረሰብ ክፍል የተውጣጡ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችም መጎብኘታቸውም ተገልጿል። ጎብኚዎቹ በሰጡት አስተያየትም መታሰቢያው በአፈታሪክ ብቻ ከልጅ ልጅ ሲሻገር የነበረዉን ታላቅ ድል ምናብ ከሳች በሆነ መልኩ ሳይሸራረፍ ለትውልድ የሚያሻግር ቅርስ ሆኖ እንዳገኙት ገልጸዋል። በአድዋ ድል ኢትዮጵያውያን ያሳዩትን ጽናት፣ አንድነትንና ህብረትን ለቀጣዩ ትውልድ ይተላለፍ ዘንድም መታሰቢያው ማስተማሪያ ሆኖ መቆሙን ተናግረዋል። የኢትዮጵያዊያን ብሎም የጥቁር ህዝቦች ድል ኩራት የሆነውን የዓድዋ ድል ታሪክ ገላጭ በሆነ መልኩ በጥራት በመሰነዱ ሀገሪቱ በመስዋትንት የተገኘች ሀገር መሆኗን በማመላከት በትውልዱ ላይ የሀገር ፍቅር ስሜት ማስረፅ ከማስቻሉም በላይ ዳር ድንበሩን ለማስጠበቅ የተቆርቋሪነት ስሜት እንዲኖረው ያስችላል ብለዋል፡፡ በጉብኝቱ የተሳተፉ ተማሪዎች በሰጡት አስተያየት የኢትዮጵያዊን ድል ብሎም የአፍሪካዊያን ኩራት የሆነው የዓድዋ ድል ታሪክ በቃል ከተማሩት በላይ የዘመኑን ትውስታ በሚጭር መልኩ በመታሰቢያው መመልከታቸውን ገልጸዋል፡፡ የዩንቨርሲቲ የታሪክ መምህራን በበኩላቸው የድል መታሰቢያው የታሪክን እውነትነት ዛሬ ላይ እንደሆነ አድርጎ ከማሳየቱም በላይ በተለይም ለታሪክ ተማሪዎች፣ለምሁራን፣ለፀሃፍት፣ለውጭ ሀገር ጎብኚዎች እና ለመሰል አካላት ሁሉ ምስል ከሳች በሆነ መልኩ እንደ ቤተ ሙከራ ሊያገለግል የሚችል ውድ ቅርስ ነው ብለዋል፡፡
የህክምና ተመራቂ ተማሪዎች እውቀታቸውንና ክህሎታቸውን በየጊዜው በማሻሻል ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠት ይገባቸዋል - ጤና ሚኒስቴር
Mar 16, 2024 101
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ የህክምና ተመራቂ ተማሪዎች እውቀታቸውንና ክህሎታቸውን በየጊዜው በማሻሻል ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎት መስጠት እንዳለባቸው የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር አየለ ተሾመ ገለፁ። የካቲት 12 ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ በተለያዩ የህክምና ዘርፎች ያሰለጠናቸውን 202 የህክምና ባለሙያዎች ዛሬ በዓድዋ ድል መታሰቢያ አስመርቋል። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር አየለ ተሾመ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የዜጎችን ጤንነት ለመጠበቅ በበሽታ መከላከልና ለታካሚዎች የተሻለ የህክምና አገልግሎት ለመስጠት በትኩረት እየተሰራ ነው። በተለይም የእናቶችንና የህፃናትን ሞት ለመቀነስ በተከናወነው ስራ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ተናግረዋል። የሀገርን እድገት ለማፋጠን ጤናማና አምራች ዜጋ ወሳኝ በመሆኑ፤ ተመራቂዎች እውቀታቸውንና ክህሎታቸውን በየጊዜው በማሻሻል ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎት መስጠት እንደሚገባቸው አሳስበዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ዮሀንስ ጫላ፥ በከተማ አስተዳደሩ ለጤና አገልግሎት ተደራሽነት ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። መንግሥት በዝቅትኛ የኑሮ ሁኔታ የሚገኙና ከፍለው መታከም የማይችሉ ዜጎችን ወጪ እየሸፈነ የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ እያደረገ መሆኑንም አስረድተዋል። ደረጃቸውን የጠበቁ አዳዲስ ሆስፒታሎች እየተገነቡ ነው ያሉት ዶክተር ዮሀንስ፥ በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ኃይል ማፍራትም ቀዳሚ ሥራ ነው ብለዋል። ከዚህ አኳያ የዛሬ ተመራቂ ተማሪዎች በኮሌጁ ያገኙትን እውቀት በተግባር በማሳየት ህብረተሰቡን ማገልገል እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል። የየካቲት 12 ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ዋና ፕሮቮስት ዶክተር ኤልያስ ተዋበ ኮሌጁ የሚሰጠውን የህክምና አገልግሎት ከማስፋት ባለፈ ብቁ የህክምና ባለሙያዎችን ለማፍራት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ሚናውን ለማስፋትም ኮሌጁን ወደ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ለማሳደግ ሂደት መጀመሩን ጠቁመዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት ተመራቂዎች ዶክተር እንዳለው ሙላቴና ዶክተር ረድኤት ፀጋዬ በትምህርት ያገኙትን እውቀትና ክህሎት በመተግበር ሀገርንና ህዝብን ለማገልገል ዝግጁ ነን ብለዋል።
በመዲናዋ ለትራፊክ አደጋ አጋላጭ የሆኑ የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገዶች ማሻሻያ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል - የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች
Mar 16, 2024 76
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ ለትራፊክ አደጋ አጋላጭ የሆኑ የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገዶች ማሻሻያ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ጠየቁ። የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን በበኩሉ የተሻለ የመንገድ ደኅንነት ለመፍጠርና የተሳለጠ የትራንስፖርት እንቅስቃሴ እንዲኖር የነባር መንገዶች ማሻሻያ እየተከናወነ ነው ብሏል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የመዲናዋ ነዋሪዎች እንደገለጹት፤ ነባር መንገዶች የከተማዋን እድገት ታሳቢ ተደርገው የተገነቡ ባለመሆናቸው የማሻሻያ ግንባታ ያስፈልጋቸዋል። ለአብነትም ከአዲሱ ገበያ በተለምዶ ሶስት ቁጥር ማዞሪያ ተብሎ እስከሚጠራው አካባቢ ያለው የፍጥነት መንገድ ለእግረኞች በቂ መሸጋገሪያ የሌለው በመሆኑ ለትራፊክ አደጋ እያጋለጠ መሆኑን ገልጸዋል። አቶ ወንድወሰን መከተ እና ወጣት ሁሴን ሱልጣን፥ መንገዱ የገበያ ስፍራና የተለያዩ የማህበራዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ያሉበት እንደመሆኑ የእግረኛ መሸጋገሪያ በቅርብ ርቀት ሊገነባ እንደሚገባው አንስተዋል። በመሆኑም በመዲናዋ የተጀመረው የነባር መንገዶች ማሻሻያ በእነሱ አካባቢም እንዲቀጥል የጠየቁ ሲሆን፥ የፍጥነት መገደቢያ፣ የትራፊክ መብራትና የመሸጋገሪያ ድልድይ ቢሰራ መልካም ነው ይላሉ። በተለምዶ 3 ቁጥር ማዞሪያ እየተባለ በሚጠራው የመዲናዋ አካባቢ ያገኘናቸው ነዋሪዎች በበኩላቸው፥ በከተማዋ እየጨመረ ካለው የህዝብና የተሽከርካሪ ቁጥር አንጻር የትራፊክ ፍሰቱን ለማሳለጥ ወቅቱን የዋጀ የመንገድ ማሻሻያ ሊደረግ እንደሚገባ ገልጸዋል። አሥር አለቃ በንቲ ተሰማ እና አቶ ቢኒያም ዳኜ እንደሚሉት፥ ነባር መንገዶች እና አካፋዮች ለእግረኛና ለተሽከርካሪ በቂ ፍሰት የማይሰጡ በመሆናቸው የትራፊክ አደጋ እየደረሰ ነው ብለዋል። የከተማ አስተዳደሩ የጀመረው የመንገድ ማሻሻያ ስራ ለችግሮች ምላሽ የሚሰጥ በመሆኑ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም ጠቁመዋል። የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ እያሱ ሰለሞን፥ የተሻለ የመንገድ ደኅንነት በመፍጠር የተሳለጠ የትራንስፖርት እንቅስቃሴ እንዲኖር የማሻሻያ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ባለፉት አምስት ዓመታት ከ190 ኪሎ ሜትር በላይ የእግረኛ መንገድ ማሻሻያ ግንባታ መደረጉን ጠቅሰዋል። የትራፊክ ፍሰት ላይ ጫና የሚፈጥሩ አደባባዮችን በመለየት በትራፊክ መብራት የመተካት ሥራ በስፋት በማከናወን የትራንስፖርት እንቅስቃሴዎችን የማሳለጥ ሥራ በመከወን ላይ መሆኑን አስረድተዋል። የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ የፍጥነት ወሰን መገደቢያና የእግረኛ መንገድ ማሻሻያ፣ የመንገድ ማስፋፊያና የአዳዲስ ድልድዮች ግንባታ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የመንገድ መሰረተ ልማቶችን ለታለመላቸው ዓላማ ብቻ በማዋል ረጅም ጊዜ እንዲያገለግሉ እንዲሁም የትራንስፖርት ፍሰትን ለማሳለጥና የትራፊክ አደጋን ለመቀነስ ሁሉም ኃላፊነቱን እንዲወጣ ጠይቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል በመስቀል አደባባይ የሚያከናውኑት የፀሎት ፕሮግራም የተወሰኑ መንገዶች ለተሸከርካሪ ዝግ ይሆናሉ - የአዲስ አበባ ፖሊስ
Mar 16, 2024 71
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል በመስቀል አደባባይ የሚያከናውኑት የፀሎት ፕሮግራም ተጀምሮ እስከሚጠናቀቅ የተወሰኑ መንገዶችን ለተሸከርካሪ ዝግ እንደሚሆኑ የአዲስ አበባ ፖሊስ አስታወቀ፡፡ አሽከርካሪዎች እንደተለመደው ለትራፊክ ፖሊሶች ትዕዛዝ ተባባሪ እንዲሆኑም ጠይቋል፡፡ በዚህም ዕሁድ መጋቢት 8 ቀን 2016 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በመስቀል አደባባይ ከሰዓት በኋላ ከቀኑ 7፡30 እስከ 12፡00 ሰዓት ድረስ የፀሎት መርሐ-ግብሩ እስከሚጠናቀቅ ድረስ የተወሰኑ መንገዶች ለተሽከርካሪ ዝግ ይሆናሉ ብሏል፡፡ አሽከርካሪዎች ሌሎች አማራጭ መንገዶችን በመጠቀም ለትራፊክ ፖሊስ አባላት ትዕዛዝ ተባባሪ እንዲሆኑም ነው ፖሊስ ጥሪውን ያስተላለፈው፡፡ በዚህም መሰረት ፦ • ከቅዱስ ኡራኤል አደባባይ ወደ መስቀል አደባባይ ለሚጓዙ ተሽከርካሪዎች ኡራኤል አደባባይ ላይ • ከቦሌ ጌቱ ኮሜርሻል አቅጣጫ ወደ መስቀል አደባባይ ኦሎምፒያ አደባባይ በታች እና በላይ እንዲሁም ግራና ቀኝ • የቀድሞው አራተኛ ክፍለ ጦር (ጥላሁን አደባባይ ላይ) • ከለገሀር መብራት ወደ መስቀል አደባባይ ለሚጓዙ ለገሀር መብራት ላይ • ከሀራምቤ መብራት ወደ መስቀል አደባባይ ሃራምቤ መብራት ላይ • ከብሔራዊ ቤተ መንግስት ወደ መስቀል አደባባይ ብሔራዊ ቤተ መንግስት አጠገብ ዕሁድ መጋቢት 8 ቀን 2016 ዓ.ም ከጠዋቱ 4፡ 00 ጀምሮ ፕሮግራሙ እስከሚጠናቀቅ ድረስ መንገዶቹ ለጊዜው ለተሽከርካሪ ዝግ ይሆናሉ ብሏል፡፡ ፕሮግራሙ በሚከናወንበት ዙሪያ እና በአካባቢው በግራና በቀኝ ለረጅምም ሆነ ለአጭር ጊዜ ተሽከርካሪ አቁሞ መሄድ ፍፁም የተከለከለ መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ጨምሮ ገልጿል፡፡
የማህበረሰብ ጤና መድህን ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ የሕክምና አገልግሎቶችን እንድናገኝ እያገዘን ነው -ተጠቃሚዎች
Mar 16, 2024 70
ሐዋሳ፤ መጋቢት 7/2016 (ኢዜአ) ፡- የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አባል መሆናችን ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቁ የሕክምና አገልግሎቶችን ጭምር በሆስፒታሎች እንድናገኝ አድርጎናል ሲሉ በሲዳማ ክልል የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች ገለጹ። አስተያየታቸውን የሰጡት በክልሉ ማዕከላዊ ሲዳማ ዞን ዳሌ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ኡራጎ ኡምቡሎ ከሦስት ዓመት በፊት የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን አባል መሆናቸውን ይገልጻሉ። በዓመት አንድ ጊዜ በሚከፍሉት ጥቂት ገንዘብ ከጤና ኬላ እስከ ሪፈራል ሆስፒታል ከፍተኛ ወጪ የሚጠይቅ የሕክምና አገልግሎት ጭምር ለማግኘት እንደረዳቸው ተናግረዋል። የጤና መድህን ተጠቃሚ መሆናቸው የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ጤና ለመጠበቅ እንዳስቻላቸውም ነው የገለጹት። በዚህም እሳቸውን ጨምሮ የአካባቢያቸው ነዋሪዎች የጤና መድህን አባልነታቸውን በወቅቱ በማሳደስ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በጤና መድህን አባልነታቸው ባለቤታቸውንና ልጃቸውን በሃዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል እንዳሳከሙ የገለጹት አርሶ አደር ኡራጎ፣ የጤና መድህን አገልግሎት አባል ባይሆኑ የህክምና ወጪውን ለመሸፈን ይቸገሩ እንደነበር ገልጸዋል። በሃዋሳ ከተማ የሚኖሩት ወይዘሮ ዘሪቱ ባሳ በበኩላቸው እንዳሉት ለጤና መድህን አገልግሎት በዓመት አንድ ጊዜ በሚከፍሉት አነስተኛ ገንዘብ እሳቸውን ጨምሮ ሁሉም የቤተሰብ አባል በቂ የሕክምና አገልግሎት እያገኙ ነው። የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ከሆኑ አራት ዓመት እንደሆናቸውና በመድሀኒት አቅርቦት በኩል አልፎ አልፎ ከሚስተዋል እጥረት በስተቀር የጎላ ችግር እንዳልገጠማቸው ገልጸው፣ ሁሉም የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ቢሆን ከፍተኛ ወጪ ይቀንሳል ብለዋል። በይርጋለም አጠቃላይ ሆስፒታል የቀዶ ህክምና አገልግሎት እንዳገኙ የተናገሩት ሌላኛው የእዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ቦጋለ ጊሳሶ በበኩላቸው፣ የማህበረሰብ ጤና መድህን አገልግሎት የአርሶ አደሩን ህይወት እየታደገ ነው ብለዋል። ለአገልግሎቱ የህብረተሰቡ ግንዛቤ በመጨመሩ የአባላት ቁጥር እያደገ መሆኑን ጠቁመው፣ ለጤና መጠበቅ ያለውን ጥቅም የተረዳን ሌሎችም አባል ሆነው እንዲጠቀሙ እየቀሰቀስን ነው ሲሉ ገልጸዋል። በሀዋሳ ከተማ ቱላ ክፍለ ከተማ በሚገኘው የሃዌላ ቱላ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ያገኘናቸው የማህበረሰብ ጤና መድህን ተጠቃሚው አቶ ሙሴ ቶማቶ በበኩላቸው ያለባቸውን የስኳርና የደም ግፊት በሽታ ለመከታተል በየጊዜው ወደ ጤና ተቋሙ እንደሚመጡ ገልጸዋል። በሆስፒታሉ ተገቢው የህክምና ክትትል እንደሚደረግላቸውና ብዙ ጊዜም የታዘዘላቸውን መድሃኒት በተመጣጣኝ ዋጋ እንደሚያገኙ ተናግረዋል። በሆስፒታሉ አልፎ አልፎ የመድሃኒት እጥረት ሲያጋጥም ከውጭ ለሚገዙት መድሃኒት ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚጠየቁም አክለዋል። በኢትዮጵያ ጤና መድን አገልግሎት የሀዋሳ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ አሰፋ ላንሳሞ በበኩላቸው በሲዳማ ክልል በሚገኙ ሁሉም ወረዳዎች የማህበረሰብ ጤና መድህን አገልግሎት ተደራሽ መደረጉን ገልጸዋል። የህብረተሰቡ ግንዛቤ እያደገ በመምጣቱ በአሁኑ ወቅት የአባልነት ምጣኔው 68 ከመቶ በላይ መድረሱን ጠቁመው፣ "በፊት የምርት ጊዜን ጠብቆ ብቻ ይታከም የነበረው አርሶ አደር አሁን በማንኛውም ጊዜ መታከም ችሏል" ብለዋል። የጤና መድህን አርሶ አደሩ ከልማቱ ሳይደናቀፍ ጤናማና አምራች ዜጋ እንዲሆን በማድረግ በኩል አስተዋጾ እያደረገ መሆኑን ነው የገለጹት። በሃገር አቀፍ ደረጃ ከ1 ሺህ 22 በሚበልጡ ወረዳዎች ተግባራዊ በተደረገው የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን አገልግሎት ከ54 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ተጠቃሚ እንደሆነ መዘገቡ ይታወሳል።