ማህበራዊ
በጣና ገባር ወንዞች ሙላት ምክንያት በሚከሰት የጎርፍ አደጋ የሚደርሰውን ጉዳት ለመከላከል እየተሰራ ነው-የአማራ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ
Jul 26, 2024 202
ባህር ዳር ፤ ሐምሌ 19/2016 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የጣና ሐይቅ ገባር በሆኑ ወንዞች ሙላት ምክንያት በሚከሰት የጎርፍ አደጋ በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት እዳይደርስ ለመከላከል ኮሚቴ ተቋቁሞ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ አስታወቀ። በደቡብ ጎንደር ዞን አስተዳደር የጎርፍ አደጋን ለመከላከል የተሰሩ የዝግጅት ሥራዎችን በማስመልከት ዛሬ መግለጫ ተሰጥቷል። የቢሮው ሀላፊ ዶክተር ማማሩ አያሌው በዚህ ወቅት የሚቲዎሮሎጂ መረጃን ዋቢ አድርገው እንደገለጹት፤ የክረምቱ የዝናብ ሁኔታ ከፍተኛና እየጨመረ የሚሄድ ነው። በመሆኑም በጣና ሐይቅ ዙሪያ በሚገኙ ደራ፣ ፎገራ እና ሊቦ ከምከም ወረዳዎች ሥር የሚገኙና ለጎርፍ ተጋላጭ የሆኑ 21 ቀበሌዎች መለየታቸውን ገልጸዋል። አደጋውን ለመከላከል በቅንጅት ሲስራ መቆየቱን ጠቅሰው፣ በዚህም ከ31 ኪሎ ሜትር በላይ የውሃ መፋሰሻ ትቦ መስራት መቻሉን ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ በጎርፍ አደጋ ችግሮች ቢከሰቱ ፈጥኖ ምላሽ ሊሰጥ የሚችል ኮሚቴ ተቋቁሞ እየተሰራ ነው ብለዋል። የደቡብ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ጥላሁን ደጀኔ በበኩላቸው እንዳሉት ደራ፣ ፎገራ እና ሊቦ ከምከም ወረዳዎች በየዓመቱ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ ናቸው።   ከዚህ ቀደም ችግሩን ቀድሞ ለመከላከል የተሰሩ ሥራዎች ለውጥ እያመጡ መሆናቸውንም ገልጸዋል። ዘንድሮም የጎርፍ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል ስጋት በመኖሩ ለዝግጅት ሥራው ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በተለይ በርብ እና ጉማራ ወንዝ መሙላት ምክንያት በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች ለችግር ሊጋለጡ ይችላሉ የሚል ስጋት ስላለ ቀድሞ ለመከላከል እየተሰራ ነው ብለዋል። በበጋ ወቅት ችግሩን ለመከላከል ከተሰሩ ሥራዎች በተጨማሪ በአሁኑ ወቅትም እየተከናወኑ ያሉ የዝግጅት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስረድተዋል። በዛሬው እለትም በዞኑ ችግሩ ሊከሰትባቸው ይችላል ተብለው በተለየቱ አካባቢዎች ለሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎች የውሃ ማከሚያ ኬሚካል ከክልሉ ውሃና ኢነርጅ ቢሮ ድጋፍ መደረጉን አስታውቀዋል።  
የአመራርነት ብቃት ያላቸውን ዜጎች ወደ ፊት ለማምጣት እየተሰራ ነው - ኤርጎጌ ተስፋዬ(ዶ/ር)
Jul 26, 2024 129
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ የአመራርነት ብቃት ያላቸውን ወጣቶች፣ ሴቶችና አካል ጉዳተኞች ወደ ፊት ለማምጣት እየተሰራ መሆኑን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እና የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ በጋራ መስራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል።   የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ(ዶ/ር) ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከተሰጡት በርካታ ተግባርና ሃላፊነቶች መካከል የሴት አመራሮችን አቅም ማጎልበትና ተጠቃሚነታቸውን ማረጋገጥ እንደሚገኝበት ተናግረዋል፡፡ ሴት አመራሮችን ወደ ፊት በማምጣት የመሪነት ሚና እንዲጫወቱ ለማስቻል ባለፉት አምስት አመታት በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያን ልማትና ብልጽግና እውን ለማድረግ የዜጎችን ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት ማረጋገጥ አንዱና ዋነኛው መንገድ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም ከአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ጋር የሚደረጉ ስምምነቶች የሴቶችን፣ ወጣቶችንና አካል ጉዳተኞችን ተጠቃሚነትና ተሳታፊነት ከማጠናከር ባለፈ አቅማቸውን ለማጎልበት የሚያግዙ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ወጣቶች የመሪነት ሚናቸውን መጫወት እንዲችሉ በአመራርነት ብቃት ያላቸውን ወጣቶች ወደ ፊት የማምጣት ስራ እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት አቶ ዛዲቅ አብርሃ በበኩላቸው፤ ለሀገሪቱ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጥ አካዳሚው ሰፋ ያሉ የሪፎርምና ትራንስፎርሜሽን ፕሮግራሞችን ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   በሀገራችን የሴቶች፣ ወጣቶችና አካል ጉዳተኞችን ችግር ለመቅረፍ ከተፈለገ ከሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር መስራት ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ ባለፉት ስድስት ወራት ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ጋር ዝግጅት ማካሄዳቸውን በማስታወስ የዛሬው ስምምነት ፕሮግራሙን ወደ ተግባር የሚያስገባ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በፕሮግራሙ ሴቶችን ለአመራርነት ማብቃት የሚያስችሉና በሌሎች ሀገራት ውጤታማ ሆኑ 10 የአመራር ማብቂያ ዘዴዎች ተግባራዊ እንደሚደረጉ አክለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የወጣቶች ሀገር መሆኗን ተከትሎ በሀገሪቱ ሁለንተናዊ ለውጥና እድገት ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ አላቸው ብለዋል፡፡ አመራርነት ልምድና ክህሎትን የሚጠይቅ መሆኑን ጠቅሰው በቀጣይም በማህበረሰብ ለውጥ ውስጥ ብቃት ያላቸው ወጣቶችን ማዘጋጀት አስፈላጊ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በዚህ ረገድ ማዕከሉ አበክሮ እየሰራ አንደሚገኝም አቶ ዛዲግ ጨምረው ገልጸዋል፡፡    
ባለፉት አምስት ዓመታት 3 ሚሊየን ዜጎች የክረምት ነፃ የበጎ ፍቃድ ህክምና አገልግሎት ተጠቃሚ ሆነዋል- ጤና ሚኒስቴር
Jul 26, 2024 128
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ባለፉት አምስት ዓመታት በክረምት ነፃ የህክምና የበጎ ፍቃድ አገልግሎት 3 ሚሊየን ዜጎች ተጠቃሚ መሆናቸውን የጤና ሚኒስቴር ገለፀ። በተያዘው በጀት ዓመት በመላ አገሪቱ ለሁለት ወራት በሚሰጠው የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት ለ 2 ሚሊየን ዜጎች ነፃ የሕክምና አገልግሎት እንደሚሰጥ ተጠቅሷል። በበጎ ፍቃድ የሚከናወነው ሀገር አቀፍ ነፃ የክረምት የጤና ምርመራ፣ የምክርና የሕክምና አገልግሎት መርኃ ግብር በቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ህክምና ኮሌጅና በኤካ ኮተቤ አጠቃላይ ሆስፒታል አስተባባሪነት በየካ ክፍለ ከተማ ዛሬ ተጀምሯል።   በመርኃ ግብሩ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ፣ የጤና ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የአርማወር ሀንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ ፣የጤና ተቋማት አመራሮችን ጨምሮ የተለያዩ እንግዶች ተገኝተዋል። ከነፃ የህክምና አገልግሎት በተጨማሪ በአነስተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኙ ዜጎች የቤት እድሳትና የትምህርት መሳሪያዎች ድጋፍ እንዲሁም የችግኝ ተከላ መርሃግብርም በዛሬው እለት ተከናውኗል። በክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት የደም ልገሳና በተለያዩ ሆስፒታሎች ተበላሽተው አገልግሎት መስጠት ያቆሙ የህክምና ቁሳቁሶች ጥገና እንደሚካሄድም ተገልጿል ። በመርሃግብሩ ማስጀመሪያ ላይ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ እንዳሉት፤ በሁለቱ ሆስፒታሎች የሚሰጠው ነፃ የህክምና አገልግሎት ከሐምሌ 19 ቀን እስከ ሐምሌ 26 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ የሚሰጥ ሲሆን በዚህም 100 ሺህ ታካሚዎች አገልግሎት እንደሚያገኙ ገልፀዋል። በተያዘው በጀት ዓመት በመላ አገሪቱ ለሁለት ወራት በሚሰጠው የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት ለ 2 ሚሊየን ዜጎች ነፃ የጤና አገልግሎት ይሰጣል። ከጤና አገልግሎቱ ባሻገር ሚኒስቴሩ ከተጠሪ ተቋማት ጋር በመሆን ግማሽ ሚሊየን ችግኞችን እንደሚተክልና ከሚተከሉት መካከል ለህክምና ግብዓት የሚሆኑና ለምግብነት የሚውሉ መኖራቸውንም ተናግረዋል። የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ህክምና ኮሌጅ ዋና ፕሮቮስት ዶክተር ሲሳይ ስርጉ በበኩላቸው ለአንድ ሳምንት በሚቆየው የነፃ ህክምና የበጎ አድራጎት አገልግሎት 30 አይነት የቅድመ ምርመራና ህክምናዎች እንደሚሰጡ ተናግረዋል።   በነፃ ህክምና አገልግሎቱ በየቀኑ ከ 7 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ በአጠቃላይ ለ 50 ሺህ ዜጎች የህክምና አገልግሎት ለመስጠት ታቅዷል ብለዋል። የኤካ ኮተቤ አጠቃላይ ሆስፒታል ዋና ስራ አስኪያጅ ዶክተር ሙሉቀን ተስፋዬ በበኩላቸው፤ በክረምት ነፃ የበጎፍቃድ አገልግሎት የተለያዩ የጤና ምርመራና ህክምና ለመስጠት መታቀዱን ተናግረዋል።   በበጎፍቃድ አገልግሎቱ ከግል የጤና ተቋማት ጋር በመተባበር የሲቲ ስካንና ኤምአርአይ አገልግሎቶችን ጨምሮ የተለያዩ ህክምና አገልግሎቶች በክፍለ ከተማው ይሰጣል ብለዋል። በተጨማሪም በዛሬው እለት ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጎችን ቤት የማደስ ተግባር እንደሚከናወን ገልፀው፤ ቤቶቹን እስከ አዲስ አመት መግቢያ ድረስ ለነዋሪዎቹ ለማስረከብ መታቀዱንም ጠቁመዋል። የቤት እድሳት ተጠቃሚ የሆኑት ወይዘሮ መስታወት ቸሩ ቤታቸው በላያቸው እንዳይወድቅ በስጋት ውስጥ እያሉ የቤት እድሳት መርሃ ግብር ተጠቃሚ መሆናቸው እፎይታ እንደሰጣቸው ተናግረዋል።   በፅዳት ስራ የሚተዳደሩት ወይዘሮ እህተፃድቅ ዘነበ የቤት እድሳቱ ለዘመመ ቤታቸው መፍትሄ የሚሰጥ እንደሆነ ተናግረዋል። የነፃ ህክምና አገልግሎት በተለይ ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ላሉ ዜጎች መፍትሄ የሚሰጥ መሆኑን የገለፁት ደግሞ በነፃ በጎፍቃድ መርሃግብሩ ህክምና ሲያገኙ ያነጋገርናቸው ታካሚዎች ዮናታን አለማየሁ፣ ደስታ አዱኛና ትዕግስት በሻዳ ናቸው።    
የተለያዩ ተቋማት በጎፋ ዞን ድንገተኛ የመሬት መንሸራተት አደጋ ጉዳት ላስከተለባቸው ቤተሰቦች ድጋፍ አደረጉ
Jul 26, 2024 131
ሶዶ፣ ሐምሌ 19/2016 (ኢዜአ)፦ የጋሞና ኮሬ ዞኖች እንዲሁም የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ በጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ የደረሰው ድንገተኛ የመሬት መንሸራተት አደጋ ጉዳት ላስከተለባቸው ወገኖች ድጋፍ አደረጉ። በጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ በሰሞኑ በተከሰተ የመሬት መንሸራተት አደጋ ሳቢያ በሰው ህይወትና ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱ ይታወቃል። የጋሞ ዞን የስራ ሃላፊዎችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍል ተወካዮች ጉዳቱ በደረሰበት ቀበሌ በመገኘት ተጎጂዎችን አጽናንተዋል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባይነህ አበራ በዚሁ ጊዜ ከተጎጂዎች ጎን መሆኑን ለማሳየት በስፍራው መገኘታቸውን ገልጸዋል።   በዚሁ መሰረት ከ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ምግብ ነክና ሌሎች ቁሳቁሶች እንዲሁም ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን በላይ የጥሬ ገንዘብ ድጋፍ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። ድጋፉም 608 ኩንታል በቆሎን ጨምሮ ሌሎች ምግብ ነክ ድጋፍና አልባሳትን ያካተተ መሆኑን ጠቅሰዋል። ሌላኛው ድጋፍ ያደረገው የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ሲሆን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ጉቼ ጉሌ (ዶ/ር) ዩኒቨርሲቲው ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት የምግብና ምግብ ነክ ድጋፍ ማድረጉን ተናግረዋል። የተደረገው ድጋፍ የመጀመሪያ ዙር መሆኑን ጠቁመው በቀጣይም የተጎዱ ወገኖችን የመደገፍ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። በተመሳሳይ የኮሬ ዞን ኃላፊዎችና የህብረተሰብ ክፍል ተወካዮች በጎፋ ዞን ተገኝተው ተጎጂ ቤተሰቦችን ያፅናኑ ሲሆን ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ቁሳቁስ ድጋፍ አድርገዋል። ድጋፉን የተረከቡት የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ፣ የተለያዩ ተቋማት እያሳዩ ለሚገኙት አጋርነት በዞኑ ስም ምስጋና አቅርበዋል። አደጋው የከፋ ጉዳት ማስከተሉን ጠቅሰው ጉዳት የደረሰባቸውን ዜጎች የመደገፍ ስራ በተቀናጀ መልኩ እየተከናወነ እንደሚገኝም አመላክተዋል።
የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከነገ ጀምሮ ለ3 ቀናት የሚቆይ ብሔራዊ ሐዘን አወጀ
Jul 26, 2024 128
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በጎፋ ዞን ገዜ ወረዳ የደረሰውን የመሬት መንሸራተት አደጋ ተከትሎ ሕይወታቸው ላለፉ ዜጎች የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከነገ ጀምሮ ለ3 ቀናት የሚቆይ ብሔራዊ ሐዘን አውጇል። የውሳኔው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፦ በደቡብ ኢትዮጵያ በጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ በተከሰተ በመሬት መንሸራተት በደረሰ አደጋ ምክንያት ሕይወታቸው ያለፈውን ነዋሪዎች በማስመልከት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተላለፈ ውሳኔ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በደቡብ ኢትዮጵያ በጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ በተከሰተው የመሬት መንሸራተት አደጋ ሕይወታቸውን ላጡ ዜጎች የተሰማውን ከፍተኛ ሀዘን በተለያየ መንገድ እየገለፀ መሆኑ ይታወቃል። አሁንም ለወዳጅ ዘመዶቻቸው እና ለመላው የአገራችን ሕዝቦች መጽናናትን እየተመኘ ብሔራዊ የሐዘን ቀን እንዲታወጅ ወስኗል። በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የሰንደቅ ዓላማ አዋጅ ቁጥር 654/2001ን ለማሻሻል በወጣው አዋጅ ቁጥር 863/2006 አንቀጽ 22 ንዑስ አንቀጽ 2 መሠረት አስፈላጊ ሆኖ በተገኘበት የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት የሀዘን ቀን የማወጅ ሥልጣን የተሰጠው ሲሆን የሰንደቅ ዓላማ አዋጅ ቁጥር 863/2006 አንቀፅ 2 ንዑስ አንቀፅ /2/ መሠረት ምክር ቤቱ በሥራ ላይ በማይኖርበት ጊዜ የተፈጠረ ክስተት ከሆነ የብሔራዊ የሀዘን ቀንና ሰንደቅ ዓላማው ዝቅ ብሎ የሚውለበለብበትን ሁኔታ በምክር ቤቱ አፈ-ጉባኤ የሚወሰን መሆኑን ይደነግጋል። በመሆኑም ከሐምሌ 20 ቀን 2016 ዓ/ም ጀምሮ ለ3 ቀናት በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ በተከሰተው የመሬት መንሸራተት አደጋ ምክንያት ሕይወታቸውን ላጡ ወገኖቻችን በማሰብ ብሔራዊ የሀዘን ቀን ሆኖ እንዲታወጅና በእነዚህ ቀናት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ በሁሉም የሀገሪቱ ግዛቶች፤ በኢትዮጵያ መርከቦች፤ በኢትዮጵያ ኤምባሲዎችና ቆንስላ ጽ/ቤቶች የሪፐብሊኩ ሰንደቅ ዓላማ ዝቅ ብሎ እንዲውለበለብ ተወስኗል።
የቁልቢ ቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል ያለምንም የፀጥታ ችግር ተከብሮ መጠናቀቁ ተገለጸ
Jul 26, 2024 94
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን እምነት ተከታዮች ዘንድ በታላቅ ድምቀት የተከበረው የቁልቢ ቅዱስ ገብርኤል በዓለ-ንግስ ያለአንዳች የፀጥታ ችግር በሰላም ተከብሮ መጠናቀቁን የምስራቅ ኢትዮጵያ አጎራባች ክልሎች የጋራ ፀጥታ ግብረ-ኃይል ገለጸ። በዓሉ በድምቀት ተከብሮ እንዲጠናቀቅ ሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ምሥራቅ ፈጥኖ ደራሽ ፖሊስ፣ ብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት፣ የድሬዳዋ ፖሊስ፣ የምስራቅና ምዕራብ ሐረርጌ ፖሊስ፣ የሐረሪ ክልል ፖሊስ፣ የምስራቅ እና ምዕራብ ኦሮሚያ እንዲሁም የሚሊሻ ኃይሉ ጋር የጋራ ዕቅድ በማውጣትና ከቤተክርስቲያኗ አባቶች ጋር በመምከር ከቅድመ ዝግጅት ጀምሮ በዓሉ ያለ ምንም የፀጥታ ችግር እንዲጠናቀቅ ሰፊ ስራዎች መሰራታቸውን ግብረ-ኃይሉ ገልጿል፡፡ በዓሉን ለማክበር በመጡ ምዕመናን ላይ አንዳንድ የሞባይል ስርቆት ወንጀል በፈፀሙ አካላት ላይ በተቋቋመው ፈጣን ችሎት አማካኝነት ከአንድ ዓመት ከሁለት ወር እስከ አንድ አመት ከስምንት ወር የሚደርስ የቅጣት ውሳኔ የተላለፈባቸው መሆኑን የጋራ ፀጥታ ግብረ-ኃይሉ መግለጹን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ መረጃ አመልክቷል።
የመልካ ቁንጡሬ ባልጪት የአረኪዮሎጂ እና ፓሊዮንቶሎጂ ሥፍራ በዓለም ቅርስነት ተመዘገበ
Jul 26, 2024 73
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ የመልካ ቁንጡሬ ባልጪት የአረኪዮሎጂ እና ፓሊዮንቶሎጂ ሥፍራ በዓለም ቅርስነት በዩኔስኮ ተመዘገበ፡፡ በሕንድ ኒው ዴልሂ እየተካሄደ በሚገኘው 46ኛው የዩኔስኮ የዓለም ቅርስ ማዕከል ዓመታዊ ጉባዔ የመልካ ቁንጡሬ ባልጪት የአረኪዮሎጂ እና ፓሊዮንቶሎጂ ሥፍራ ሶስት መስፈርቶችን በማሟላት የዓለም ቅርስ ሆነ ተመዝግቧል፡፡ ሥፍራውን በዓለም ቅርስነት ያበቁት መስፈርቶች፦ ከ2.5 ሚሊየን ዓመት እስከ መጨረሻው የድንጋይ ዘመን የሰው ልጅ ይጠቀምባቸው የነበሩ የድንጋይ መገልገያዎች ይዞ የሚገኝ በመሆኑ፡፡ እስከ 2.5 ሚሊየን ዓመት እድሜ ያላቸው የተለያዩ የሰውና የእንስሳት ቅሪተ አካሎች በብዛት የሚገኙበት በመሆኑ:: የሰው ልጅ ከድንጋይ የተለያዩ መገልገያዎችን/መሳሪያዎችን ይሰራ እንደ ነበር የሚያሳዩ ስምንት የባልጩትና ሌሎች የድንጋይ መሳሪያ ማምረቻ ሥፍራዎችን ይዞ የሚገኝ በመሆኑ ነው፡፡ የቱሪዝም ሚንስትር አምባሳደር ናሲሴ ጫሊ ለጉባኤው በላኩት መልእክት ይህ ቅርስ የተመዘገበው ሉሲ የተገኘችበትን 50ኛ አመት በምናከብርበት ወቅት መሆኑ ለሀገራችን ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን ገልፀዋል:: በእርግጥም ሀገራችን ምድረ ቀደምት መሆኗን ለአለም ተጨማሪ ማረጋገጫ የሰጠ መሆኑንም አንስተዋል:: ይህ ቅርፅ ተጠብቆ እንዲቆይም የኢትዮጵያ መንግስት አስፈላጊውን ሁሉ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል:: መልካ ቁንጡሬ ባልጪት ከአዲስ አበባ ወደ ቡታጂራ በሚወስደው ጎዳና 50 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ አዋሽ ወንዝ ዳርቻ ላይ የሚገኝ ሲሆን ኢትዮጵያ በዩኔስኮ ካስመዘገበቻቸው ቋሚ የሚዳሰሱ ቅርሶች 12ኛው መሆኑንም የቱሪዝም ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርና የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ በጋራ ለመስራት ስምምነት ተፈራረሙ
Jul 26, 2024 69
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርና የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ በሴቶች፣ ወጣቶችና አካል ጉዳተኛ ዜጎች አቅም ግንባታ ዙሪያ በጋራ ለመስራት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ(ዶ/ር) እና የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት አቶ ዛዲግ አብርሃ ተፈራርመዋል።   የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትሯ በስምምነት ስነ-ስርዓቱ ላይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የሴቶች፣ ወጣቶችና አካል ጉዳተኛ ዜጎችን መብት ለማስከበር፣ በየዘርፉ ያላቸውን እኩል ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እና በየደረጃው ለማብቃት ከተለያዩ ባለድርሻና አጋር አካላት ጋር እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ሚኒስቴሩ ከዚህ ቀደም ከአካዳሚው ጋር በጋራ በፌዴራልና በክልል የሚገኙ ሴት አመራሮችን ውሳኔ ሰጪነት ሚና ለማሳደግ የአቅም ግንባታ ፕሮግራሞችን በመቅረፅ ተግባራዊ ሲያደርግ መቆየቱን ገልፀዋል። ስምምነቱ የአስፈጻሚ አካላትን አቅም በመገንባት የአፍሪካ የብልፅግና ተምሳሌት የሆነች ኢትዮጵያን ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ውስጥ የአመራር ብቃት ያላቸውና የመሪነት ሚና የሚጫወቱ ሴቶች፣ ወጣቶችና አካል ጉዳተኛ ዜጎችን ለማፍራት ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። ማዕከሉ ከኢትዮጵያ ባለፈ ለአፍሪካ ሀገራት ተምሳሌት ሊሆን የሚችል ትልቅ ስራ እየሰራ እንደሚገኝ ገልፀው ስምምነቱ ወደ ተግባር እንዲሸጋገር እና ስኬታማ እንዲሆን ትኩረት ሰጥቶ በቅንጅት ይሰራል ብለዋል። የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት አቶ ዛዲግ አብርሃ በበኩላቸው አካዳሚው አቅምን ለመገንባት የሚያስችሉ የአመራር ልማት ፕሮግራም፣ የአመራር የልህቀት ሽልማት፣ የመሠረተ ልማት እና የጋራ የጥናትና ምርምር ስራዎችን ከአጋር አካላት ጋር በመቀናጀት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል። የአቅም ግንባታ ስልጠናዎቹ እንደ ሀገር የሚስተዋለውን የአመራር ክፍተት ለመሙላት እና በተለይ ተተኪ ወጣት አመራሮችን ለማፍራት እንደሚያግዝ መግለጻቸውን ከሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃው ያመለክታል።
የወባ በሽታን ለመከላከል የሚደረገውን ጥረት መገናኛ ብዙሀን ግንዛቤን በመፍጠር እንዲያግዙ ተጠየቀ 
Jul 26, 2024 76
ሆሳዕና ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የወባ በሽታ ስርጭትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚደረገውን ጥረት መገናኛ ብዙሀን የህብረተሰቡን ግንዛቤ በማሳደግ እንዲያግዙ ተጠየቀ። የክልሉ ጤና ቢሮ የወባ በሽታን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚካሄዱ ተግባራትን ለማጠናከር የመገናኛ ብዙሀን ሚናን በተመለከተ ያዘጋጀው የምክክር መድረክ በወራቤ ከተማ እየተካሄደ ነው። በዚህን ጊዜ የክልሉ ጤና ቢሮ ኃላፊ አማካሪ አቶ ሀብቴ ገብረሚካኤል እንዳሉት በክልሉ የወባ በሽታ ስርጭትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የተለያዩ ሥራዎች እየተሰሩ ነው። የአካባቢ ንጽህናን መጠበቅና ውሃ ያቆሩ አካባቢዎችን ተከታትሎ ከማፍሰስ ባለፈ የኬሚካል እርጭትና ሌሎች ሥራዎችም እየተሰሩ ነው ብለዋል። እነዚህ ተግባራት የተፈለገውን ውጤት እንዲያመጡ የማህበረሰቡ ግንዛቤ ሊጎለብት ይገባል ያሉት አቶ ሀብቴ፣ በዚህ ረገድ የመገናኛ ብዙሀን ተቋማት ወጥ በሆነ መልኩ በህብረተሰቡ ላይ ግንዛቤን በመፍጠር የበኩላቸውን እገዛ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።   የወባ በሽታ የሚያስከትለውን ሁለንተናዊ ተፅዕኖ ለማስቀረት ህብረተሰቡን በማስገንዘብ በኩል ተቋማቱ ከፍተኛውን ድርሻ እንደሚወስዱም ነው ያስገነዘቡት። የክልሉ የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ማሙሽ ሁሴን በበኩላቸው እንዳሉት፣ በክልሉ የወባ በሽታን ጨምሮ ሌሎች ተላላፊና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት እየተሰራ ነው። በዚህም ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ጠቁመው፣ ለአብነትም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ ተከስተው የነበሩ የኮሌራ እና የኩፍኝ በሽታዎችን ጫና ሳያሳድሩ መቆጣጠር መቻሉን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የወባ በሽታ ዳግም የማገርሸት ባህሪ እያሳየ መሆኑን ገልጸው፣ ይህን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት የመገናኛ ብዙሀን አካላት የህብረተሰቡን ግንዛቤ በማሳደግ እንዲያግዙ አሳስበዋል። የወባ በሽታ ስርጭትን ለመከላከል ስጋት የሆኑ አካባቢዎችን ለይቶ ማህበረሰቡን በማሳተፍ በልዩ ክትትል ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑንም ገልጸዋል። በዚህም በክልሉ በ30 ወረዳዎች የኬሚካል እርጭት ሥራ የተከናወነ ሲሆን ከአንድ ሚሊዮን በላይ የአልጋ አጎበር ስርጭት መካሄዱንም ተናግረዋል። በተጨማሪም ውሃ አቆር አካባቢዎችን የማፅዳት ሥራ ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ መቀጠሉን ነው የተናገሩት። የመገናኛ ብዙሀን ተቋማት የወባ በሽታ የሚያስከትለውን ጫና ለመከላከልና ለመቆጣጠር ለህብረተሰቡ ግንዛቤን በመፍጠር የበኩላቸውን እንዲወጡም አስገንዝበዋል። ለአንድ ቀን በተዘጋጀው በዚሁ የምክክር መድረክ ላይ የተለያዩ መገናኛ ብዙሀን ተቋማት አመራሮችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው።    
ዓመታዊው የቁልቢ ገብርኤል የንግስ በዓል በሰላም መጠናቀቁን የምስራቅ ሐረርጌ ዞን ፖሊስ አስታወቀ
Jul 26, 2024 66
ሐረር፣ ሐምሌ 19/2016 (ኢዜአ)፡-ዓመታዊው የቁልቢ ገብርኤል ንግስ በዓል በሰላም መጠናቀቁን የምስራቅ ሐረርጌ ዞን ፖሊስ አስታወቀ። የምስራቅ ሐረርጌ ዞን ፖሊስ አዛዥና ጊዜያዊ የፀጥታ ግብረ ሃይል ሰብሳቢ ኮሚሽነር ናስር መሐመድ እንደገለጹት፤ ዓመታዊው የንግስ በዓሉ በርካታ የእምነቱ ተከታዮችና እንግዶች በተገኙበት በሰላም ተከብሮ ተጠናቋል። የዘንድሮ የሐምሌ ገብርዔል ንግስ በዓል አንድም የወንጀል ድርጊት ያልተፈፀመበትና የትራፊክ አደጋ ያልተመዘገበበት ሆኖ መጠናቀቁንም ተናግረዋል። የወንጀል ድርጊቶችና የትራፊክ አደጋ መከላከል የተቻለው ምዕመናኑ በተለያዩ መገናኛ ዘዴዎች የተላለፉትን የጥንቃቄ መልዕክቶች ተግባራዊ በማድረጋቸው መሆኑን አስረድተዋል። እንዲሁም በስፍራው የተሰማራው የጸጥታ ሃይልና በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ባከናወኑት የተቀናጀ ሥራ ከፍተኛውን ድርሻ ማበርከቱን ነው ኮሚሽነር ናስር ያመለከቱት። በተለይ የአካባቢው ነዋሪዎች ምዕመናኑ ወደ በዓሉ መምጣት ከጀመሩበት ዕለት ጀምሮ ለእንግዶች ላደረጉት መልካም አቀባበልና መስተግዶ ምስጋና አቅርበዋል። የተከናወነው የጸጥታ ስራም የተቀናጀና የተፈለገውን ግብ መምታቱን የጠቆሙት ኮሚሽነር ናስር፣ ምዕመናኑም ወደየመጡበት ሥፍራ ጥንቃቄ በተሞላበት ሁኔታ በማሽከርከር እንዲመለሱ አሳስበዋል። በበዓሉ ላይ የተገኙት ምዕመናን በዓሉ መጠናቀቁ ወደየመጡበት አካባቢ በመመለስ ላይ ናቸው።  
በሶማሌ ክልል የፍትህ ተቋማትን በማጠናከር መልካም አስተዳደርን ለማስፈን የተጀመረው  ጥረት ይጠናከራል - የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት
Jul 26, 2024 72
ጅግጅጋ፣ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፡-በሶማሌ ክልል የፍትህ ተቋማትን በማጠናከርና የባለሙያዎችን አቅም በመገንባት መልካም አስተዳደርን ለማስፈን የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት መሐመድ ባሩድ አስታወቁ፡፡ የክልሉ ምክር ቤት በጅግጅጋ ከተማ ሰባተኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ ነው። የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት መሐመድ ባሩድ በጉባኤው ላይ ባቀረቡት ሪፖርት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የፍትህ ተቋማት ለሕብረተሰቡ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲሰጡ በማደራጀትና የባለሙያዎችን አቅም በመገንባት ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል። በዚህም በየደረጃው ያሉትን የፍትህ ተቋማት በሚገባ ለማደራጀትና የሕግ ባለሙያዎችን የማስፈጸም አቅም ለማጎልበት እንዳስቻለ አስረድተዋል። በቀጣይም በክልሉ በአጭርና ረጅም ጊዜ ስልጠናዎች የባለሙያዎችን የማስፈጸም አቅም በማሳደግ፣ የፍትህ አገልግሎት ማሻሻያ ፕሮግራምን ሥራ ላይ በማዋል፣ ኅብረተሰቡን የተሟላ ፍትህ ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚሰራ አስታውቀዋል።   ፍርድ ቤቱ በበጀት ዓመቱ ከቀረቡት ከ11ሺህ በላይ የክስ መዝገቦች ውስጥም ከ9 ሺህ በላይ የሚሆኑ ውሳኔ ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ከነዚህ ውስጥ ሰባት ሺህ በላይ የሚሆኑት የፍትሐ ብሄር ጉዳዮች፣ ቀሪዎቹ ደግሞ የወንጀል ክሶች መሆናቸውን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ የስነ-ምግባር ግድፈት የታየባቸው ስድስት ዳኞች ከስራ መሰናበታቸውን ፕሬዚዳንቱ አስታውቀዋል። የምክር ቤቱ አባላት በሪፖርቱ ላይ በሰጡት አስትያየት በወረዳ ፍርድ ቤቶች የሚታየው የዳኞች እጥረት፣ ምቹ የሥራ አካባቢ አለመኖርና የውሳኔ መዘግየት ችግሮች እንዲፈቱ አሳስበዋል። ምክር ቤቱ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱን የስራ እንቅስቃሴ ሪፖርት በሙሉ ድምፅ አጽድቋል። የክልሉ ምክር ቤት ከትናንት በስቲያ ማካሄድ የጀመረውን ጉባዔ ዛሬ ያጠናቅቃል ተብሎ ይጠበቃል።
ሜጀር ጀኔራል ተስፋዬ አያሌው እና አቶ ተስፋዬ  ንዋይ ለአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት መጻሕፍት አበረከቱ
Jul 26, 2024 106
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ ሜጀር ጀኔራል ተስፋዬ አያሌው እና አቶ ተስፋዬ ንዋይ ለአብርሆት ቤተ-መጻሕፍት 350 መፅሐፍትን አበረክተዋል። መፅሐፍቶቹን የአብርሆት ቤተ መፅሐፍ ዳይሬክተር ኢንጂነር ውብአየሁ ማሞ ተረክበዋል። በመከላከያ ህብረት ዘመቻ ዋና መምሪያ የኃይል ሥምሪትና ክትትል መምሪያ ኃላፊ ሜጀር ጄነራል ተስፋዬ አያሌው በቅርቡ "የጀግንነት ሥነ ልቦና" በሚል ርዕስ ለንባብ ያበቁትን መፅሐፍ ለአብርሆት ቤተ መፅሐፍት አስረክበዋል፡፡   መፅሐፍቱ በቁጥር 200 ሲሆኑ በአማርኛ፣ በአፋን ኦሮሞ፣ በሶማሌኛ እና በእንግሊዘኛ ቋንቋዎች የተዘጋጁ ናቸው። ትውልዱ ይህንኑ መፅሐፍት በማንበብና የጀግንነት ስነ ልቦና በመላበስ ለሀገሩ ሁለንተናዊ ስኬት የበኩሉን እንዲወጣ ያግዛል ብለዋል። ተማሪዎች የክረምት ጊዜያቸውን በአብርሆት ቤተ መፅሐፍት በማሳለፍ የንባብ ባህላቸውን እንዲያዳብሩ ጥሪ አቅርበዋል። የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተስፋዬ ንዋይ በበኩላቸው በራሳቸው የተፃፉ የፍትህ ጉዳይ፣ የመሬት ሕግ እና አተገባበርን ጨምሮ የአመራር ክህሎት ርዕስ ያላቸውን 150 መፅሐፍትን ለአብርሆት ቤተ መፃሕፍት ማበርከታቸውን ተናግረዋል። ዛሬ ያበረከቷቸውና ከዚህ ቀደም ለቤተ መፅሐፍቱ የሰጧቸው መፅሐፍቶች በአብርሆት በኩል ለበርካታ አንባቢያን ተደራሽ መሆን እንደሚችሉ ገልጸዋል። ዛሬ ለአብርሆት ቤተ መጽሃፍት የተበረከቱት መፅሐፍቶች በፍትህ ጉዳይ፣ በመሬት ሕግ እና አተገባበርን ጨምሮ በአመራር ክህሎት እውቅት የሚያስጨብጡ ናቸው ብለዋል። የአብርሆት ቤተ መፅሕፍት ዳይሬክተር ኢንጂነር ውብአየሁ ማሞ የተበረከቱት መፅሐፍቶች ትውልድን በጀግንነት፣ በፍትህና በአመራርነት ክህሎት በመገንባት ረገድ ከፍተኛ አበርክቶ አላቸው ብለዋል። ለተደረገው ድጋፍ በማመስገን ሌሎች አካላትም ለቤተ መፅሐፍቱ ድጋፋቸውን እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።              
በክረምት የህክምና በጎ ፍቃድ አገልግሎት ለ 2 ሚሊየን ዜጎች ነፃ የጤና አገልግሎት ይሰጣል-የጤና ሚኒስቴር
Jul 26, 2024 86
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016 (ኢዜአ)፦በመላ አገሪቱ ለሁለት ወራት በሚሰጠው የክረምት ህክምና በጎ ፍቃድ አገልግሎት ለ 2 ሚሊየን ዜጎች ነፃ የጤና አገልግሎት እንደሚሰጥ የጤና ሚኒስትር መቅደስ ዳባ ዶክተር ገለፁ። በበጎ ፍቃድ የሚከናወነው ሀገር አቀፍ ነፃ የክረምት የጤና ምርመራ፣ የምክርና የሕክምና አገልግሎት መርኃ ግብር በቅዱስ ጳውሎስ ሚሊኒየም ህክምና ኮሌጅ ዛሬ ተጀምሯል። በመርኃ ግብሩ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ፣ የጤና ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የአርማወር ሀንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር አፈወርቅ ካሱ ፣የጤና ተቋማት አመራሮችን ጨምሮ የተለያዩ እንግዶች ተገኝተዋል። በበጎ ፍቃድ አገልግሎቱ ከነፃ ህክምና በተጨማሪ የደም ልገሳ፣ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ ዜጎች የቤት እድሳትና የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ እንዲሁም የችግኝ ተከላ እንደሚካሄድ ተገልጿል ። በዚሁ ወቅት የጤና ሚኒስትሯ መቅደስ ዳባ የነፃ ህክምና በጎ ፍቃድ አገልግሎቱ በዛሬው እለት በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ህክምና ኮሌጅና ኤካ ኮተቤ አጠቃላይ ሆስፒታል መጀመሩን ተናግረዋል፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃ ለሁለት ወራት እንደሚካሄድ ጠቁመዋል። ለሁለት ወራት በሚቆየው የክረምት ህክምና በጎ ፍቃድ አገልግሎት ለ 2 ሚሊየን ዜጎች ነፃ የጤና አገልግሎት እንደሚሰጥ የጤና ሚኒስትሯ ገልጸዋል። የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ህክምና ኮሌጅ ዋና ፕሮቮስት ዶክተር ሲሳይ ስርጉ በበኩላቸው ለአንድ ሳምንት በሚቆየው የነፃ ህክምና የበጎ አድራጎት አገልግሎት 30 አይነት የቅድመ ምርመራና ህክምናዎች እንደሚሰጡ ተናግረዋል። በነፃ ህክምና አገልግሎቱ በየቀኑ ከ 7 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ በአጠቃላይ ለ 50 ሺህ ዜጎች የህክምና አገልግሎት ለመስጠት ታቅዷል ብለዋል።  
ኢሉ አባቦርን ዞንን ከቱሪዝም ሀብቱ ተጠቃሚ ለማድረግ መስኅቦችን የማልማትና የማስተዋወቅ ስራ በትኩረት እየተከናወነ ነው
Jul 26, 2024 66
መቱ ፤ ሐምሌ 19/2016 (ኢዜአ)፡- ኢሉ አባቦርን ዞንን ከቱሪዝም ሀብቱ ተጠቃሚ ለማድረግ መስኅቦችን የማልማትና የማስተዋወቅ ስራ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ባሕልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ተፈጥሯዊ፣ ታሪካዊ እና ባሕላዊ መስኅቦችን ለማስተዋወቅ በተሰሩ ስራዎች ተስፋ ሰጪ ውጤቶች መመዝገባቸው የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ወንድሙ ደበላ ለኢዜአ አስታውቀዋል። በዚህም በዞኑ የሚገኙ መስኅቦችን በመለየት በተሰራው የሚስተዋወቅ ስራ በርካታ ሰዎች የሶር ፏፏቴ መጎብኘታቸውን ገልጸዋል። በኦሮሚያ ክልል ደረጃ የዓለም ቱሪዝም ቀን በስፍራው እንዲከበር በማድረግም ተጨማሪ የማስተዋወቅ ስራ መሰራቱን ተናግረዋል። በተጨማሪም የኢትዮጵያ አስጎብኚዎች ማኅበር አባላትን ጨምሮ ሌሎች በቱሪዝም ዙሪያ የሚሰሩ አካላትን ወደ ዞኑ በማምጣት መስኅቦቹን እንዲጎበኙ መደረጉንም ተናግረዋል። በዚህም በዓመቱ ወደ ዞኑ የመጡ እንግዶችና የመንግሥት አካላት ሶር ፏፏቴን ጨምሮ የተለያዩ መስህቦችን መጎብኘታቸውን ገልጸዋል።   በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከዘርፉ የተሻለ ገቢ መገኘቱን የተናገሩት ኃላፊው፣ መስህቦቹን በማልማትና በማስተዋወቅ የዞኑን ማኅበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። ከዚሁ ጎን ለጎን መስኅቦቹን በማልማቱ በኩል በተሰሩት ስራዎች በዞኑ በቾ ወረዳ ወደ ሶር ፏፏቴ የሚወስድ 5 ኪሎ ሜትር፣ በአሌ ወረዳ ወደሚገኝ ታሪካዊ ስፍራ የሚወስድ 17 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገዶች መሰራታቸውን ገልጸዋል። በዞኑ ባለፈው ዓመት የተቋቋመው ፓርክም የተለያዩ የዱር እንስሳት ዝርያዎች፣ አዕዋፋት፣ መልክዓ ምድርና የደን ዛፎች ዝርያዎች ያሉበት ሲሆን፣ በዞኑ የቱሪዝም ሀብት ላይ ተጨማሪ አቅም መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ የሶር ፏፏቴን ጨምሮ ሌሎች ተፈጥሯዊ መስህቦች ከሚገኙባቸው ወረዳዎች አንዱ በሆነው የበቾ ወረዳ መስህቦቹን ማልማት ስራ እይተከናወነ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የወረዳው ባሕልና ቱሪዝም ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተመስገን ወንድሙ ናቸው። በተለይም ሶር ፏፏቴን ለሚጎበኙ ቱሪስቶች በአግባቡ ለማስተናገድ የሚያግዝ የእንግዳ መቀበያ መገንባቱን ተናግረዋል። በሌላ በኩል የሶር ፏፏቴን በመጠበቅና በማስተዋወቅ ስራ ላይ ወጣቶችን በአስጎብኚነት ጭምር በማደራጀት የስራ ዕድል ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑን አቶ ተመስገን አስታውቀዋል።    
በድሬዳዋ  የ8ኛ ክፍል አስተዳደር አቀፍ ፈተና ከባለፈው አመት የተሻለ ውጤት ተመዝግቧል - የአስተዳደሩ ትምህርት ቢሮ
Jul 26, 2024 68
ድሬዳዋ ፤ ሐምሌ19/2016(ኢዜአ)፡- በድሬዳዋ የስምንተኛ ክፍል አስተዳደር አቀፍ ፈተና ከባለፈው አመት የተሻለ ውጤት መመዝገቡን የአስተዳደሩ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ። በአስተዳደሩ ዘንድሮ በተሰጠው የ8ኛ ክፍል ፈተና 62 ነጥብ 4 በመቶ የሚሆኑት ተማሪዎች ማለፋቸውንም ገልጿል። የአስተዳደሩ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሱልጣን አልይ ዛሬ በሰጡት መግለጫ በ2016 ዓ.ም በአስተዳደር አቀፍ የተሰጠውን የ8ተኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና ከወሰዱት 9ሺህ 85 ተማሪዎች መካከል 5ሺህ 673 ተማሪዎች ወደ ዘጠነኛ ክፍል ማለፋቸውን ገልጸዋል። ያለፉት ተማሪዎች ከጠቅላላ ተፈታኞች 62 ነጥብ 4 በመቶ መሆናቸውን ጠቁመው፣ የዘንድሮ የ8ተኛ ክፍል ፈተና ማለፊያ ውጤት 50 በመቶና እና ከዚህ በላይ መሆኑን ተናግረዋል። ይሁንና ለአካል ጉዳተኞች 45 እና ለሴት ተማሪዎች ደግሞ 47 በመቶ እንዲሆን መወሰኑን አስታውቀዋል። በዘንድሮው የስምንተኛ ክፍል አስተዳደር አቀፍ ፈተና ከአምናው አንፃር የተሻለ ውጤት የተመዘገበበት መሆኑንም አቶ ሱልጣን ተናግረዋል። "አምና የማለፊያ ነጥብ 40 በመቶ በነበረበት ወቅት ያለፉት ተማሪዎች 38 በመቶ ብቻ ናቸው" ያሉት አቶ ሱልጣን፣ የትምህርት ጥራትና ውጤትን ለማስጠበቅ ዘንድሮ የማለፊያ ውጤቱ ከፍ እንዲል መደረጉን ገልጸዋል። መምህራን ያደረጉት ያለሰለሰ ጥረት ለውጤቱ መሻሻል ከፍተኛ ድርሻ እንዳለውም ጠቁመዋል። በተጨማሪም የትምህርት ስብራትን ለመጠገን ከፍተኛ አመራሩ፣ የትምህርት አመራሮች፣ ቤተሰቦችና ባለድርሻ አካላት ያደረጉት ርብርብ አበርክቶው የጎላ መሆኑን አስረድተዋል። ለውጡን ለማጠናከርና የትምህርት ጥራትን ለመጠበቅ የሚከናወኑ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። ተማሪዎች የፈተና ውጤታቸውን ከዛሬ ጀምሮ በተለያዩ አማራጮች መመልከት እንደሚችሉም ታውቋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት አቅጣጫ መሰረት ተጎጂዎችን የመደገፍና የማቋቋም ስራ በትኩረት እየተከናወነ ነው - አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም(ዶ/ር)
Jul 26, 2024 116
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 19/2016(ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሰጡት አቅጣጫ መሰረት በጎፋ ዞን በገዜ ጎፋ ወረዳ በመሬት መንሸራተት አደጋ ለተጎዱ ወገኖች ከሰብዓዊ ድጋፍ ጀምሮ የመልሶ ማቋቋም ስራው በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን አስታወቀ። የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት በጎፋ ዞን በገዜ ጎፋ ወረዳ ሀምሌ 15/2016 በተከሰተው የመሬት መንሸራተት አደጋ የተጎዱ ወገኖችን የመደገፍ ስራው ተጠናክሮ ቀጥሏል። ይሄንን ተከትሎም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት አቅጣጫ መሰረት የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ያሉበት ቡድን በአካባቢው ተገኝቶ ማህበረሰቡን የማፅናናት፣ የሰብዓዊ ድጋፍ ፍላጎቶችና ትኩረት የሚሹ ጉዳዮችን የመለየት ስራ አከናውነዋል፡፡ የህይወት አድን ስራው እየቀጠለ በሚገኝበት በዚህ ወቅትም የ226 ዜጎች ህይወት እንደጠፋ የተረጋገጠ ሲሆን ፍለጋውም መቀጠሉን ጠቁመዋል። የተፈናቃይ ቁጥርን በሚመለከት በአደጋው ክስተት ዙሪያ እንዲነሱ የተደረጉትን 600 ሰዎችን ጨምሮ በቀጣይ መነሳት ያለባቸው ተጨማሪ 6 ሺህ የሚጠጉ ተጋላጮች የተለዩ መሆናቸውን አስረድተዋል። አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም(ዶ/ር) እንደገለጹት ከሰብዓዊ ድጋፍ ተግባራት ጎን ለጎን የመልሶ ማቋቋም ስራዎች በተደራጀና በባለሙያ ጥናት በሚለይ ቦታ ለማከናወን ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ ነው። እየተደረገ ያለው ሰብዓዊ ድጋፍም ከክልሉ መስተዳደር፣ ከዞኖችና ከማህበረሰብ በተጨማሪ ከፌዴራል መንግስት አካላት፣ ከሌሎች የክልል መስተዳደሮች፣ ተቋማትና ዜጎች ተጠናክሮ የቀጠለ ሲሆን አጋር አካላትም በዩ.ኤን ኦቻ አስተባባሪነት ምግብና ምግብነክ ያልሆኑ ድጋፎች እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከአጭር ጊዜ አኳያ ለሚከናወኑ የህይወት አድንና መልሶ የማቋቋም ስራዎች ፈፃሚ አካላት የተለዩ ሲሆን የአሰቸኳይ ጊዜ አደጋ ምላሽ የማስተባበርና የማቀናጀት አደረጃጀትም ተፈጠሯል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን አደጋው ከተከሰተበት እለት ጀምሮ ኢትዮጵያዊነትን አጉልቶ ያሳየ ሰብዓዊ ድጋፍ ሁሉንም አካላት አመስግኗል። ችግሩንም በዘላቂነት ለመፍታት በሚደረገው ርብርብ ድጋፋችሁ እንዳይለይ ከወዲሁ እንጠይቃለን ሲሉም ገልጸዋል፡፡
የሲዳማ ክልል በገዜ ጎፋ ወረዳ በመሬት መንሸራተት አደጋ ለተጎዱ ወገኖች የአይነትና የገንዘብ ድጋፍ አደረገ
Jul 26, 2024 73
ሀዋሳ፤ ሀምሌ 19/ 2016 (ኢዜአ)፦የሲዳማ ክልል መንግስት በጎፋ ዞን ገዜ ጎፋ ወረዳ በተከሰተ የመሬት መንሸራተት አደጋ ለተጎዱ ወገኖች የሚሆን ከ8 ሚሊዮን ብር በላይ የአይነትና የገንዘብ ድጋፍ አደረገ። የክልሉ የአደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ አበራ ዊላ በአደጋው ለተጎዱ ወገኖች የሚሆን ከ8 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ ወደስፍራው መላኩን ገልጸዋል። የክልሉ ምንግስት ከሦስት ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን ምግብና ምግብ ነክ የሆኑ ድጋፎችን እንዲሁም በቼክ 5 ሚሊዮን ብር ድጋፍ መላኩን ተናግረዋል።   ህብረተሰቡንና የተለያዩ አካላትን በማስተባበር የተሰበሰበውን ድጋፍ የሚያደርስ ቡድን ወደ ስፍራው መንቀሳቀሱንም ገልጸዋል። ከቡድኑ ጋር የሕክምና ባለሙያዎችም አብረው መላካቸውን ኮሚሽነሩ አክለው ገልጸዋል። የአሁኑ ሰብአዊ ድጋፍ የመጀመሪያ መሆኑን የገለጹት አቶ አበራ የክልሉ መንግስትና ህዝብ ተጎጂዎችን የመደገፉ ሥራ በቀጣይም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም