ማህበራዊ
አስቸኳይ እርዳታ ለሚሹ ዜጎች ሰብዓዊ ድጋፍ ተደራሽ የማድረጉ ስራ ተጠናክሮ ቀጥሏል-የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን 
Apr 27, 2024 19
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2016(ኢዜአ)፦ አስቸኳይ እርዳታ ለሚሹ ዜጎች ሰብዓዊ ድጋፍ ተደራሽ የማድረጉ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም (ዶ/ር) ገለጹ። የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም (ዶ/ር) በተለያዩ አካባቢዎች እየተከናወነ ያለውን የሰብአዊ ድጋፍና ተደራሽነትን በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋ ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች የዓይነትና የገንዘብ ድጋፍ በተጠናከረ መልኩ እየቀረበ መሆኑንም ገልፀዋል። የሰብአዊ ድጋፉ በየሩብ ዓመቱ እንደሚሰራጭ ጠቅሰው ከጥር እስከ መጋቢት ድረስ ለ6 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዜጎች ድጋፍ ሲደረግ መቆየቱን ጠቁመዋል። አሁን ባለንበት ወቅትም ከሚያዝያ አንስቶ እስከ ሰኔ ከስምንት ሚሊዮን በላይ ዜጎች የሰብአዊ ድጋፍ ተደራሽ የማድረጉ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ድጋፉ በመንግስትና በአጋር አካላት ትብብር እንደሚከናወንም እንዲሁ። በአጠቃላይ ከሚያዚያ እስከ ሰኔ ላለው ድጋፍ 11 ቢሊዮን ብር አካባቢ ወጭ የሚጠይቅ ሲሆን 5 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር የሚያወጣ ድጋፍ በመንግስት ይሸፈናል ነው ያሉት፡፡ ቀሪው በለጋሽ አካላት እንደሚሸፈንም ነው የተናገሩት፡፡ የመንግስት ዋነኛ ትኩረት አደጋን ቀድሞ መከላከል መሆኑን የተናገሩት ኮሚሽነሩ ለዚህም የተጋላጭነት ልየታ የአደጋ ስጋት ፕሮፋይል ጥናት መሰራቱን ጠቁመዋል። በሀገሪቱ ከሚገኙ ወረዳዎች ከግማሽ በላይ የሚሆኑት በዚህ ጥናት መሸፈናቸውን ተናግረዋል።  
የአፍሪካ ሕብረት ጉባኤን በስኬት በማዘጋጀት ያዳበርነውን ባሕላችንን አጠናክረን መቀጠል ይገባል - አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ
Apr 27, 2024 72
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2016(ኢዜአ)፡- የአፍሪካ ሕብረት ጉባኤን መስተንግዶ በስኬት በማዘጋጀት ያዳበርነውን ባሕላችንን አጠናክረን መቀጠል ይገባል ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ ገለጹ። መዲናችን የላቀች የዲፕሎማሲ ማዕከል ሆና እንድትቀጥል አደራ መወጣታችን የሁልጊዜ ተግባራችን ሊሆን ይገባል ሲሉም ሚኒስትሩ አስታውቀዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር 37ኛው የአፍሪካ ሕብረት መደበኛ የመሪዎች ጉባኤና 44ኛው የአፍሪካ ሕብረት ስራ አስፈፃሚዎች ጉባኤ በስኬት እንዲጠናቀቅ ጉልህ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የምስጋናና የእውቅና መርሐ ግብር አካሂዷል። የእውቅናና የምስጋና አሰጣጥ መርሃ ግብሩ በዝግጅት ብሔራዊ ኮሚቴ አማካኝነት መከናወኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል። አምባሳደር ታዬ አፅቀሥላሴ ለሀገራችን የተሰጠውን ታሪካዊ ሀላፊነትና ክብር በሚመጥን አኳኋን በተሳካ ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ያደረጉ አካላትን አመስግነዋል። የአፍሪካ ሕብረት ጉባኤ መስተንግዶ በስኬት በማዘጋጀት ያዳበርነውን ባሕላችንን አጠናክረን መቀጠል ብቻ ሳይሆን፣ መዲናችን የላቀች የዲፕሎማሲ ማዕከል ሆና እንድትቀጥል አደራ መወጣታችን የሁልጊዜ ተግባራችን ሊሆን ይገባልም ነው ያሉት ሚኒስትሩ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታና የብሔራዊ ኮሚቴ ሰብሳቢ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ በጉባኤው የተሳተፉ ከተለያዩ ሀገራት የመጡ እንግዶችን በተሳካ መልኩ ተቀብሎ በመሸኘት እንዲሁም የተሟላ አገልግሎት ለሰጡ ተቋማት ምስጋና አቅርበዋል። በእውቅና አሰጣጥ መርሀ-ግብሩ ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ እንዲከናወን አስተዋጽኦ ላደረጉ የተለያዩ ተቋማት ከአምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ የምስጋና እና እውቅና የምስክር ወርቀት ተበርክቶላቸዋል።
በደቡብ ኦሞ ዞን ከ11 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ የኮንትሮባንድ እቃዎችን መያዙን ፖሊስ አስታወቀ
Apr 26, 2024 63
ጂንካ፤ ሚያዚያ 18/2016 (ኢዜአ) ፡ - በደቡብ ኦሞ ዞን ከ11 ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያላቸው የኮንትሮባንድ ዕቃዎች መያዙን የዞኑ ፖሊስ መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የማህበረሰብ አቀፍ ወንጀል መከላከል ዲቪዥን ኃላፊ ዋና ኢንስፔክተር ጋዲ በርቂ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የኮንትሮባንድ እቃዎቹ የተያዙት የሰሌዳ ቁጥሩ ኮድ B3-65858 በሆነ አይሱዙ የጭነት ተሽከርካሪ ተደብቀው ሲጓጓዙ በነበረበት ወቅት ነው። ተሽከርካሪው በደቡብ ኦሞ ዞን ከዳሰነች ወረዳ ወደ አዲስ አበባ እየተጓዘ እንደነበረም አመልክተዋል። በወረዳው በቱርሚ እና በዲመካ ከተማ መካከል በሚገኝ ጫካ ውስጥ የሰሌዳ ቁጥሩን ለመቀየር ተሽከርካሪው በቆመበት ወቅት የኮንትሮባንድ እቃዎቹን ከነአሽከርካሪው መያዛቸውን ተናግረዋል። በተሽከርካሪው ቀደም ሲል ተለጥፎ የነበረውን የአዲስ አበባ ሰሌዳ ቁጥር በደቡብ ክልል ሰሌዳ ቁጥር ለመቀየር ሙከራ መደረጉን የገለጹት ዋና ኢንስፔክተር ጋዲ፣ ከህብረተሰቡ በደረሰ ጥቆማ መሠረት ትናንት ከሌሊቱ 6 ሰዓት ላይ በፖሊስ ሊያዝ ችሏል ብለዋል። እንደ እርሳቸው ገለጻ፤ በኮንትሮባንድ ሲጓጓዝ የተያዙት ንብረቶች 7ሺህ 288 የሞባይል ስልኮች እና 3ሺህ 140 የሞባይል ባትሪዎች ናቸው። ለኮንትሮባንድ እቃዎቹ መያዝ የህብረተሰቡና የፖሊስ ቅንጅት ፋይዳ የጎላ መሆኑን ያመለከቱት ዋና ኢንስፔክተሩ፣ የተሽከርካሪው ረዳት ለጊዜው መሰወሩን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም ፖሊስ በቁጥጥር ሥር ባደረገው አሽከርካሪ ላይ የምርመራ ሥራ መጀመሩንም ዋና ኢንስፔክተር ጋዲ ጨምረው ገልጸዋል። የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴ በአገር ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ስለሚያስከትል ኅብረተሰቡ ከፀጥታ አካላት ጎን በመቆም የጀመረውን ድጋፍ እንዲያጠናከር ጥሪ አቅርበዋል።    
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አካል ጉዳተኞች የልማት ተሳታፊና ተጠቃሚ ለማድረግ ይሰራል- አቶ እንደሻው ጣሰው
Apr 26, 2024 60
ሆሳዕና፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የአካል ጉዳተኞችን የልማት ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንደሚሰራ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው ገለጹ። ዓለም አቀፍ የአካል ጉዳተኞች ቀን "ለአካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እና ለዘላቂ የልማት ግቦች ስኬት ትርጉም ያለው ትብብር" በሚል መሪ ቃል ዛሬ በሆሳዕና ከተማ ተከብሯል። አቶ እንዳሻው በዚህ ወቅት እንዳሉት በክልሉ ሁለንተናዊ ለውጥ እንዲመጣ የሁሉም ዜጎች ቅንጅታዊ ተሳትፎ ያስፈልጋል። አካል ጉዳተኞች የሚገጥሟቸውን ተግዳሮቶች በጽናት ከመቋቋም ባለፈ ሁለንተናዊ የልማት ተሳትፎና ተጠቃሚነታቸውን እንዲያሳድጉ አስገንዝበዋል። የክልሉ መንግስት ለአካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ትኩረት መስጠቱን የገለጹት አቶ እንዳሻው፣ አካል ጉዳተኞችም ፈተናን ተቋቁመው ለክልሉ ሁለንተናዊ እድገት መሳለጥ ድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። በክልሉ አካል ጉዳተኞች ያላቸውን አቅምና እውቀት ተጠቅመው ተጠቃሚነታቸውን ማረጋገጥ የሚችሉበት ሰፊ ዕድል መኖሩንም ጠቁመዋል። ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ራሳቸውን ማብቃትና ፈተናዎችን በ"ይቻላል" መንፈስ ለማለፍ ተግተው እንዲሰሩ ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ አስገንዝበዋል። የክልሉ መንግስት የአካል ጉዳተኞችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። አካል ጉዳተኞችን የልማቱ ተሳታፊና ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የክልሉ ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሎምባ ደምሴ ናቸው። የአካል ጉዳተኞችን ሰርቶ የመለወጥ ዕሳቤን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን ጠቅሰው፣ ክህሎታቸውን የሚያሳድጉበት የማበልጸጊያ ማዕከል ለማስገንባትም እንቅስቃሴ መጀመሩን አመልክተዋል። "ሁለንተናዊ ልማት የሁሉንም ዜጎች ተሳትፎና ተጠቃሚነት መረጋገጥን ይጠይቃል" ያሉት ኃላፊው፣ በዚህ ረገድ በክልሉ ያለው ሁኔታ አበረታች ነው ብለዋል። አካል ጉዳተኞች ለመብቶቻቸው መከበር ጠንክረው መስራት እንዳለባቸው የገለጹት አቶ ሎምባ፣ የልማት ተሳትፏቸውን ለማጠናከርም መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት በቅንጅት እንዲሰሩ አስገንዝበዋል። የክልሉ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ መሐመድ ሼይቾ በበኩላቸው አካል ጉዳተኞች ከሌሎች የማህበረሰብ ክፍሎች ጋር እኩል ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታ እንዲፈጠርላቸው ጠይቀዋል። የክልሉ መንግስት ለአካል ጉዳተኞች እያደረገ ላለው ድጋፍ ያመሰገኑት ፕሬዚዳንቱ፣ በክልሉ ለሚከናወኑ ሁሉን አቀፍ የልማት ሥራዎች ስኬት የድርሻቸውን እንደሚወጡ አመልክተዋል። በተጨማሪም በዓሉን በድምቀት ለማክበር አስተዋጽኦ ያደረጉ አካላትን ፕሬዚዳንቱ አመስግነዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ ለአካል ጉዳተኞች የእጅ ድጋፍ ክራንች እና የዊልቸር ድጋፍ ተበርክቷል።
በክልሉ ከ5 ሺህ 500 ለሚበልጡ መምህራንና የትምህርት አመራሮች የሙያ ብቃት ምዘና እየተሰጠ ነው
Apr 26, 2024 70
ዲላ ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከ5 ሺህ 500 ለሚበልጡ መምህራንና የትምህርት አመራሮች የሙያ ብቃት ምዘና እየተሰጠ መሆኑን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ። በዚህ ወቅት የክልሉ ትምህርት ቢሮ ስርዓተ ትምህርት ዝግጅት ዳይሬክተርና የዲላ ማዕከል የፈተና አስተባባሪ አቶ ናታን ላብሶ እንደገለጹት፣ በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል የተለያዩ ተግባራት በመከናወን ላይ ናቸው። ለመምህራንና የትምህርት አመራሮች ዛሬ መሰጠት የተጀመረው የሙያ ብቃት ምዘና የዚሁ አካል መሆኑንም ጠቁመዋል። እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ ምዘናው በክልሉ በሚገኙ 12 የዞን ከተሞች የተጀመረ ሲሆን፣ በዚህም 5ሺህ 559 መምህራንና የዘርፉ አመራሮች ይመዘናሉ። በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተው ምዘና በማስተማር ላይ ለሚገኙ መምህራን የሚሰጥ መሆኑንም አስታውቀዋል። መምህራንና የዘርፉ አመራሮች ለፈተናው ተገቢ ትኩረት እንዲሰጡም አቶ ናታን አሳስበዋል። የጌዴኦ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ዘማች ክፍለ በበኩላቸው በምዘና ሥርዓቱ በዞኑ በ1ኛ እና መካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እያገለገሉ ያሉ 402 መምህራንና የትምህርት አመራሮች ዛሬ መፈተን ጀምረዋል ብለዋል ። ምዘናው ብቃት ያላቸውን መምህራን ወደፊት በማምጣት የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ያግዛል ብለዋል። በተጨማሪም የመምህራንን ጥቅማ ጥቅምና ሙያ ከማሻሻል ባለፈ ትውልዱን በስነ ምግባርና በእውቀት ለማነጽ የጎላ ፋይዳ እንዳለው አስረድተዋል።    
የአደጋ ስጋት አመራርን በተደራጀና በተናበበ አግባብ መምራት የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወነ ነው
Apr 26, 2024 59
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ የአደጋ ስጋት አመራርን በተደራጀና በተናበበ አግባብ መምራት የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወነ መሆኑን የአደጋ ሥጋት አመራር ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም (ዶ/ር) ገለጹ። የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን የአመራርና ሰራተኞች የቅድመ ስራ ስምሪት ስልጠና በአፍሪካ ልህቀት ማእከል ጀምረዋል።   ስልጠናው "በሪፎርም በተቀናጀ ፣ በተናበበና በተደራጀ አመራር ለአደጋ የማይበገር አገርና ማህበረሰብ መፍጠር" በሚል መሪ ቃል ነው እየተካሄደ ያለው። የስልጠናው አላማ የኮሚሽኑ አመራሮች እና ሰራተኞች ተመሳሳይ እሳቤ እና አረዳድ እንዲኖር የማነሳሳት እና የማብቃት መሆኑ ተመላክቷል። የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ኮሚሽኑ ተቋማዊ ለውጥ ለማምጣት በሚያስችል መልኩ የሪፎርም ስራዎችን እያከናወነ ነው። ከ 2005 ጀምሮ ሲያገለግል የነበረውን ፖሊሲ ማሻሻል የመጀመሪያ ስራ ተደርጎ መወሰዱን ገልጸዋል። በዚህም ፖሊሲው አዳዲስ እሳቤዎችን አካቶ በወርሀ የካቲት አጋማሽ በሚኒስትሮች ምክርቤት ጸድቆ ወደስራ መግባቱን ጠቁመዋል። ተቋማዊ አደረጃጀትን የመፈተሽ እና የመከለስ እንዲሁም የሰው ሀይሉን እንደ አዲስ በመዋቅር የሰው ሀይል የማጠናከር ስራ መሰራቱን ተናግረዋል። የአደጋ ስጋት አመራርን በተደራጀ እና በተናበበ መንገድ መምራት የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አመልክተዋል። በቅርቡ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የጸደቀው የአደጋ ስጋት አመራር ፖሊሲ የነበሩ ስብራቶችን የሚጠግን መሆኑን አብራርተዋል። ፖሊሲው የሰብአዊ ድጋፍን በራስ የመሸፈን አቅምን የሚያጎለብትና ቅጽበታዊ ችግሮች በሚያጋጥሙበት ወቅት ማንኛውንም አካል ድጋፍ ሳይጠይቅ በራስ አቅም መመለስ የሚቻልበትን ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል። አደጋ ልማት ባለበት እንዲቆም የሚያደርግና ወደ ኋላም የሚመልስ በመሆኑ በአግባቡ ተረድቶ መምራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ፖሊሲው የልማት እቅድ አካል መሆኑን ገልጸው ከልማት እና እድገት እቅድ ጋር የሚተገበር መሆኑን ጠቁመዋል። የሚኒስትሮች ምክር ቤት በቀን 16/06/2016 ዓ.ም የአደጋ ስጋት አመራር ፖሊሲን ማጽደቁ ይታወሳል።  
ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአካል ጉዳተኞችን ፍትሀዊ የልማት ተጠቃሚነት የሚያጎለብቱ ተግባራት ተከናውነዋል
Apr 26, 2024 50
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአካል ጉዳተኞችን ፍትሀዊ የልማት ተጠቃሚነት የሚያጎለብቱ የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌደሬሽን ገለፀ። የሰው ልጆች በተለያዩ የህይወት አጋጣሚዎች ተፈጥሮአዊ እና ሰው ሰራሽ በሆኑ መንስኤዎች የአካል ጉዳት ሊገጥማቸው ይችላል ። አካል ጉዳተኞች ያጋጠማቸው ችግር ሳይበግራቸው ምርታማ ሆነው ራሳቸውን፣ ቤተሰቦቻቸውን ብሎም ሀገራቸውን ለማገልገል በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ደግሞ ዘርፈ ብዙ ተግዳሮቶች ይገጥማቸዋል። አካል ጉዳተኞች ለረጅም ዘመናት ከሚያነሷቸው ችግሮች መካከል በሀገሪቱ በሚፈለገው ደረጃ ለአካል ጉዳተኞች ምቹ የሆኑ መሰረተ ልማቶች አለመኖር ይጠቀሳል። ይህን ተከትሎ መንግስት ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአካል ጉዳተኞችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ስራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛል። በአሁኑ ወቅት በከተማዋ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ማድረጉን የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌደሬሽን ዋና ዳይሬክተር አቶ አባይነህ ጉጆ ለኢዜአ ተናግረዋል፡፡ ፌደሬሽኑ አካል ጉዳተኞች የሚያነሷቸው ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎች ምላሽ የሚያገኙበትን ሁኔታ ለመፍጠር ከተለያዩ ባለድርሻ እና አጋር አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ ነው ብለዋል። በዚህም በባለፉት የለውጥ ዓመታት የአካል ጉዳተኞችን የመሰረተ ልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት በመንግስት በኩል እየተከናወኑ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል ። በሀገሪቱ የሚገነቡ መሰረተ ልማቶች በአብዛኛው ለአካል ጉዳተኞች ምቹ ላለመሆናቸው ምክንያቱ የተቋማት በቅንጅት የመስራት ልምድ ሳይጎለብት በመቆየቱ እንደሆነ አንስተዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት ችግሩ እየተቀረፈ በመምጣቱ ፌዴሬሽኑ ከተለያዩ ተቋማት ጋር የአካል ጉዳተኞችን የመሰረተ ልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚረዱ ስምምነቶች ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ በለውጡ ዓመታት የተሰሩ የልማት ስራዎች አካል ጉዳተኞች የሚገጥማቸውን ችግር ለመቅረፍ ትልቅ ሚና ቢኖራቸውም አሁንም አካል ጉዳተኛው ከሚያነሳቸው ጥያቄዎች አንጻር በርካታ የቤት ስራዎች መኖራቸውን ጠቁመዋል። መንግስት የሚሰራቸው የመሰረተ ልማት ስራዎች አካል ጉዳተኞችን ያገናዘቡ እንዲሆኑ ለጀመረው ስራ የመዲናዋ የኮሪደር ልማት ማሳያ መሆኑን በአብነት አንስተዋል። ከተማ አስተዳደሩ መዲናዋን ለነዋሪዎች ምቹ የመኖሪያ አካባቢን ለመፍጠር የጀመራቸው ስራዎችም የአካል ጉዳተኛውን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አንጻር ጉልህ ድርሻ እንዳላቸው አቶ አባይነህ አክለዋል።  
ለአውቶብስ ብቻ የተለዩ መንገዶች የብዙኀን ትራንስፖርትንት የምልልስ አቅም በማሳደግ ፍሰቱን ያሳልጣሉ
Apr 26, 2024 69
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- ለአውቶብስ ብቻ የተለዩ መንገዶች የብዙኀን ትራንስፖርትን የምልልስ አቅም በማሳደግ የትራንስፖርት ፍሰቱን እንደሚያሳልጡ የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ ። በየጊዜው የሚጨምረው የከተማዋ ነዋሪዎች ቁጥር ካለው የትራንስፖርት አማራጭ እና ብዛት ጋር አለመጣጣሙ ይጠቀሳል። የከተማ አስተዳደሩ የትራፊክ መጨናነቅና የትራንስፖርት እጥረቱን ለማቃለል የሚረዱ የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ ይገኛል።   ከነዚህ መካከል በአንዳንድ መንገዶች በስተቀኝ በኩል ከነባሮቹ አውቶብስ ማቆሚያዎች በተጨማሪ ለአውቶብስ ብቻ የሚሉ ጹሑፎች በጎልህ ተጽፈው ይታያል። ለአውቶብስ ብቻ የተለዩ መንገዶችን በተመለከተ ኢዜአ ከአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ምትኩ አስማረ ጋር ቆይታ አድርጓል። በከተማው ውስጥ ያለው የአውቶብስ ቁጥር ከአገልግሎት ፈላጊው ጋር ያለመመጣጠን እንዲሁም የተሳፋሪ ቁጥር ከጊዜ ጊዜ እየጨመረ መምጣት ችግሩን እንዳጎላው ተናግረዋል። ለአውቶብስ ብቻ የተለዩት መንገዶች የአውቶብሶችን ምልልስ በማቀላጠፍና ተሳፋሪዎችን በፍጥነት እንዲጭኑ በማድረግ ፍላጎትና አቅርቦቱን ለማመጣጠን ይረዳሉ ነው ያሉት። ለአውቶብስ ብቻ የተለዩ ቦታዎችን በመጠቀም በስራ መግቢያና መውጫ ሰዓት ላይ የአውቶብሶችን የምልልስ አቅም በመጨመር ችግሩን ለማቃለል እየሰራን ነው ሲሉ ሃላፊው ተናግረዋል። ከዊንጌት እስከ ጊዮርጊስ ለአውቶብስ ብቻ የተለዩና ቀደም ብለው የተጀመሩ ስራዎችን በቀጣይ ወደ ጀሞ ሶስት እንደሚሰፋ ገልጸዋል፡፡ መስመሮቹን ማሳደግ በራሱ የትራፊክ መጨናነቁን እንደሚያቃልልና በተጠቀሱት ቦታዎች ያለአግባብ በሚጠቀሙ አሽከርካሪዎች ላይ የቁጥጥር ስራዎች በተጠናከረ መንገድ ይሰራል ብለዋል።                                                                  
ምክር ቤቱ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት መሰረታዊ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሩን እንዲያስተካክል አሳሰበ
Apr 26, 2024 111
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት መሰረታዊ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሩን እንዲያስተካክል አሳሰበ። ቋሚ ኮሚቴው የአገልግሎቱን የ2016 በጀት የዘጠኝ ወራት የስራ አፈጻጸም ገምግሟል።   በዚሁ ጊዜ የቋሚ ኮሚቴው አባላት ተቋሙ የሲቪል ምዝገባ ቁጥጥርና ሽፋንን ለማሳደግ እየሰራቸው ያሉ ስራዎች ተስፋ ሰጪ ቢሆኑም ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ በርካታ ችግሮች እንዳሉበት አንስተዋል። ዜጎች በተቋሙ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ከፍተኛ ቅሬታ ሲያሰሙ የቋሚ ኮሚቴው አባላት በመስክ ምልከታ ጭምር ማረጋገጣቸውንም ነው የተናገሩት። ተቋሙ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ እየታየበት ያለውን ውስብስብ ችግር ከመሰረቱ ሊፈታ እንደሚገባም ነው የቋሚ ኮሚቴው አባላት ያሳሰቡት። ተቋሙ ከቴክኖሎጂ አጠቃቀምና ለተገልጋዩና ለአገልጋዩ ምቹ የሆነ የስራ ከባቢን ከመፍጠር አኳያ ክፍተቶች ያሉበት መሆኑንም ነው የቋሚ ኮሚቴው አባላት የተናገሩት። በድንበር አካባቢ ያለው የቁጥጥር ስርዓት በሚፈለገው ደረጃ ባለመሆኑ ለህገ-ወጥ የሰዎች ዝወውር መበራከት ምክንያት መሆኑንና ለዚህ ደግሞ ተቋሙ የድንበር ቁጥጥር ስርዓቱን እንዲያጠናክር ነው ማሳሰቢያ የተሰጠው። የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሰላማዊት ዳዊትና የተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች ከቋሚ ኮሚቴው አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። እንደ ዋና ዳይሬክተሯ ገለጻ፤ ተቋሙ በኢትዮጵያ ዕድሜ ጠገብ ከሆኑ ተቋማት መካከል አንዱ ቢሆንም ከቴክኖሎጂ አጠቃቀም፣ ከሰው ሃይልና ከግብዓት ጋር ተያይዞ የተከማቹ ችግሮች አሉበት ። አገልግሎቱ ካለበት የረጅም ጊዜ ውስብስብ ችግር አኳያ በአጭር ጊዜ ውስጥ መፍትሄ መስጠት አዳጋች እንደሆነ አንስተዋል። የተቋሙን አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ የሰው ሃይልና የቴክኖሎጂ አጠቃቀሙን ማሻሻል የሚያስችሉ የተለያዩ የህግና የአደረጃጀት ማሻሻያዎች እየተደረጉ መሆኑንም ነው ያብራሩት። እነዚህ ማሻሻያዎች ሙሉ ለሙሉ ተጠናቀው ወደ ስራ ሲገቡ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮች መፍትሄ ያገኛሉ ብለዋል። የድንበር አጠባበቅ ስርዓቱ ላይ ክፍተቶች መኖራቸውን ያረጋገጡት ዋና ዳይሬክተሯ ተጨማሪ በጀትና የሰው ሃይል በመመደብ አስተማማኝ ስርዓት ለመዘርጋት ስራዎች ተጀምረዋል ብለዋል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ እጽገነት መንግስቱ በበኩላቸው፣ አገልግሎቱ ከፓስፖርትና ከወሳኝ ኩነት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ በርካታ የህዝብ ቅሬታ የሚነሳበት መሆኑን ተከትሎ ችግሮችን ለመፍታት የተጀመሩ ጥረቶች የሚበረታቱ ናቸው ብለዋል። ተቋሙ ከሚሰጠው አገልግሎት አስፈላጊነት አንጻር የሚፈለገውን ትኩረት አለማግኘቱን ጠቅሰው፣ ከህግ ማዕቀፍና ከሌሎች ጉዳዮች ጋር ተያይዞ መሟላት ላለባቸው ነገሮች ቅድሚያ ሰጥቶ ሊሰራ ይገባል ብለዋል። በተቋሙ የሚያጋጥመውን ብልሹ አሰራር ማስቀረት የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም አገልግሎቱን ቀልጣፋና ዘመናዊ ማድረግ እንዳለበት ተናግረዋል። ህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን ለመከላከል የድንበር አጠባበቅ ስርዓቱን ጠንካራ ማድረግ የሚያስችሉ ስራዎችንም መስራት እንደሚገባም ሰብሳቢዋ ተናግረዋል።
ኮሚሽኑ የአደጋ ምላሽ አሰጣጥን በራስ አቅም ለመሸፈን እያከናወናቸው ያሉ ስራዎች ሊጠናከሩ ይገባል
Apr 26, 2024 88
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡ የፌደራል አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን የአደጋ ምላሽ አሰጣጥን በራስ አቅም ለመሸፈን እያከናወናቸው ያሉ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ የፌደራል ተቋማት የሱፐርቪዥን ቡድን ገለጸ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን ተቋቁሞ ትኩረት በተሰጣቸው ዘርፎች ላይ የመስክ ምልከታ እንዲደረግ አቅጣጫ ማስቀመጣቸው ይታወሳል። በዚህም መሰረት በፕላንና ልማት ሚኒስቴር አስተባባሪነት የተቋቋመው የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽንን የስራ እንቅስቃሴዎች ላይ የመስክ ምልከታ አድርጓል፡፡   በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የማህበራዊ ዘርፍ የፕላንና የመንግስት ኢንቨስትመንት ዴስክ ኃላፊ እና የሱፐርቪዥን ቡድኑ አስተባባሪ ከተማ ቱፋ፤ ኮሚሸኑ በመንግስት በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት የፖሊሲ፣ የአሰራርና የመመሪያ ማሻሻያ ማድረጉን ተመልክተናል ብለዋል፡፡ አደጋን ለመቀነስ ጠንካራ የአደጋ ስጋት ልየታ፣ ክትትል እና ትንበያ በማድረግ እየሰጠ ያለው የቅድመ ማስጠንቀቂያ አገልግሎትም የሚበረታታ መሆኑን አንስተዋል፡፡ ኮሚሽኑ በአገር አቀፍ ደረጃ ባሉት 3 ሺህ የሰብዓዊ ድጋፍ ማሰራጫ ጣቢያዎች አማካኝነት በችግር ውስጥ ለሚገኙ ዜጎች እርዳታ ተደራሽ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ የተጠቃሚ ልየታን፣ ምዝገባን እና የእርዳታ ቁሳቁስ ስርጭትን በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግም የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡ ኮሚሽኑ ዓለም አቀፍ የረድኤት ድርጅቶች እርዳታ ባቋረጡበት ወቅት የአደጋ ምላሽ አሰጣጥን በራስ አቅም ለመሸፈን የጀመራቸውን ስራዎች የሚበረታቱ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህ ስራም ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ነው ያሉት፡፡ በተመሳሳይ ኮሚሽኑ የእርዳታ እህል ማከማቻ መጋዘኖችን ደረጃ ለማሻሻል እና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል አሰራሩን በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግ የጀመረውን ጥረት አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አመላክተዋል፡፡ የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሐይዳሩስ ሃሰን በበኩላቸው፤ አሁን ላይ በቂ የሚባል የመጠባበቂያ እህል ክምችት መኖሩን ገልጸዋል፡፡ ተቋሙ ባደረገው የፖሊሲ ማሻሻያ መሰረትም ተቋማዊ አደረጃጀትና አሰራሩ በቴክኖሎጂ የተደገፈ ለማድረግ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ መንግስት ዜጎች ለችግር እንዳይጋለጡ የራስ አቅምን በመጠቀም ረገድ እያደረገ ያለው ድጋፍ አበረታች መሆኑን ገልጸው፤ ከሱፐርቪዥን ቡድኑ ለተሰጡ አስተያየቶች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት በትኩረት እንሰራለን ብለዋል፡፡  
ኢትዮጵያ እና ኮንጎ ሪፐብሊክ በአየር ትራንስፖርት ዘርፍ በጋራ መስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት ተፈራረሙ
Apr 26, 2024 62
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና ኮንጎ ሪፐብሊክ በአየር ትራንስፖርት ዘርፍ በጋራ መስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት ተፈራረሙ፡፡ ስምምነቱን የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዶክተር ዓለሙ ስሜ እና የኮንጎ ሪፐብሊክ የትራንስፖርት፣ ሲቪል አቪየሽንና መርቻንት ኔቪ ሚኒስትር ኦነሬ ሳይ ተፈራርመዋል። የትራንስፖርት እና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር ዶክተር አለሙ ስሜ፤ ስምምነቱ ሀገራቱ ግንኙነታቸውን ለማጠናከር ያላቸውን ቁርጠኝነት ያሳዩበት ነው ብለዋል።   ስምምነቱ የሁለቱን ሀገራት ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች በማጠናከር ረገድ ትልቅ ሚና ይጫወታል ብለዋል። ሁለቱን ሀገራት ከሌሎች ሀገሮች ጋር በማስተሳሰር በኩልም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው መሆኑንም ገልጸዋል። ስምምነቱ በበረራ ምልልስ፣ በመዳረሻ ቦታ፣ በትራፊክ መብቶች፣ በአውሮፕላን ዓይነት፣ በተወካይ አየር መንገዶች ቁጥር እና በመሳሰሉት ጉዳዮች ላይ ገደብ የማያስቀምጥ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአሁኑ ጊዜ ወደ ኮንጎ ሪፐብሊክ በሳምንት ሰባት በረራ የሚያደርግ ሲሆን ስምምነቱ ወደ ብራዛቪልና ፖይንትኖይር ከተሞች የሚያደርገውን በረራ በማጠናከር የአገልግሎት አድማሱን ለማስፋት ምቹ ሂደት የሚፈጥር ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በኮንጎ ሪፐብሊክ የሚገኙ የአየር መንገዶች እንዲጠናከሩ አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኗንም ጠቁመዋል። ይህም የአፍሪካ አየር መንገዶች በአፍሪካ አየር ገበያ ያላቸውን ድርሻ ከማሳደግ አንጻር ትልቅ ሚና እንደሚጫወትም ገልጸዋል። ስምምነቱን በአጭር ጊዜ ውስጥ ተግባራዊ በማድረግ የሁለቱን ሀገራት የጋራ ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንደሚሰራም ነው የተናገሩት፡፡ የአየር ትራንስፖርት ተደራሽነትና ትስስር አስፈላጊነትን በመገንዘብ ኢትዮጵያ እስካሁን ባለው ሂደት በሁሉም አህጉራት ከሚገኙ 112 ሀገሮች ጋር የአየር አገልግሎት ስምምነቶችን መፈራረሟንም ጠቁመዋል። የኮንጎ ሪፐብሊክ የትራንስፖርት፣ ሲቪል አቪየሽንና መርቻንት ኔቪ ሚኒስትር ኦነሬ ሳይ በበኩላቸው ሀገራቸው ስምምነቱን ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ ቁርጠኛ ናት ብለዋል።   ስምምነቱ የሁለቱ አገራት መሪዎች በተስማመሙት መሰረት መከናወኑን ጠቁመው ይህም የሁለቱን አገራት ግንኙነት የሚያጠናክር መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ በኢቪየሽን ዘርፍ ያላቸውን ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚሸጋግር መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያና የኮንጎ ሪፐብሊክ የረዥም ጊዜ ዲፕሎማቲክ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት መሆናቸውንም አክለዋል፡፡
በክልሉ ለአካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ የልማት ተሳትፎና ተጠቃሚነት ትኩረት ይሰጣል---አቶ እንዳሻው ጣሰው
Apr 26, 2024 60
ሆሳዕና፤ ሚያዝያ 18/2016 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ የልማት ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ የማብቃትና የመደገፍ ሥራ ይሰራል ሲሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው ገለጹ። ዓለም አቀፍ የአካል ጉዳተኞች ቀን "ለአካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እና ለዘላቂ የልማት ግቦች ስኬት ትርጉም ያለው ትብብር" በሚል መሪ ቃል ዛሬ በሆሳዕና ከተማ እየተከበረ ይገኛል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው በመርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት የአካል ጉዳተኞች የእኩል ተጠቃሚነት መብት እንዲረጋገጥ በክልሉ በተቀናጀ መንገድ ይሰራል። በክልሉ አካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ በሆነ መልኩ የልማቱ ተሳታፊና ተጠቃሚ ሆነው ራሳቸውን ከማስተዳደር ባለፈ ለሌሎች እንዲተርፉ የማብቃትና የመደገፍ ሥራ ይሰራል። ያላቸውን አቅም አውጥተው እንዲጠቀሙ ድጋፉ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው የተናገሩት። ለአካል ጉዳተኞች ምቹ የሥራ አካባቢ ከመፍጠር ባለፈ በክህሎት በማብቃት በኢኮኖሚ ዕድገት የበኩላቸውን እንዲወጡ ቅንጅታዊ ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።   የክልሉ ሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሎምባ ደምሴ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በክልሉ የአካል ጉዳተኞችን መብት ለማስጠበቅና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የተደነገጉ ህጎች እንዲተገበሩ ከማድረግ ጀምሮ የተለያዩ ሥራዎች በመከናወን ላይ ናቸው። አካል ጉዳተኞች በተለያየ መንገድ ክህሎታቸውን በማውጣት እንዲያዳብሩ የሚያግዝ ማበልጸጊያ ማዕከል ክልሉ በማስገንባት ላይ መሆኑንም ጠቁመዋል። ቢሮው ለአካል ጉዳተኞች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት መረጋገጥ ከባለድርሻ አካላት ጋር ተቀናጅቶ ይሰራል ሲሉም ገልጸዋል። በመድረኩ ላይ የአካል ጉዳተኞት ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ በሚያግዙ ሥራዎች ላይ የተዘጋጀ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሰነድ ቀርቦ ውይይት እየተደረገበት ነው። በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋጤ ሰርሞሎን ጨምሮ ሌሎች የሥራ ሃላፊዎችና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል። ዓለም አቀፍ የአካል ጉዳተኞች ቀን በሀገር አቀፍ ደረጃ ለ31ኛ ጊዜ በክልሉ ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ እየተከበረ መሆኑ ተመላክቷል።
የህንድ መንግሥት ባደረገው ድጋፍ  ለ400 ስዎች የሰው ሰራሽ የአካል ድጋፍ የተሐድሶ አገልግሎት በሎጊያ ሆስፒታል  እየተሰጠ ነው
Apr 26, 2024 73
ሠመራ ፤ ሚያዝያ 18/2016 (ኢዜአ)፦የህንድ መንግሥት ባደረገው ድጋፍ ለ400 ሰዎች የሰው ሰራሽ የአካል ድጋፍ የተሐድሶ አገልግሎት በሎጊያ ሆስፒታል እየተሰጠ ነው። በሰው ሰራሽ የተሃድሶ አገልግሎት አሰጣጥ ማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር የአፋር ክልል የኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ አቶ አሊ መሐመድ እንዳሉት በፕሮጀክቱ የተጀመረው ለአካል ጉዳተኛ ወገኖቻችን ሰው ሰራሽ አካል መሥጠት ዜጎቹ በነፃነት ከቦታ ቦታ እንዲንቀሳቀሱ የሚያስችላቸው ነው ብለዋል። ከዚህም በተጓዳኝ የቴክኖሎጂ እና የዕውቀት ሽግግር ሚና ያለው መሆኑን ጠቅሰው የህክምና ባለሙያዎችን አቅም ከማጠናከር ባሻገር ለተቋማት መጠናከር ወሳኝ ነው ብለዋል። በዚህ ዘመቻ አገልግሎቱን የሚያገኙ ወገኖችን ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሻገረ መሆኑን ጠቅሰው ለዚህ መሣካት ድጋፍ ያደረገው የህንድ መንግስት እና የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ሚኒስቴር እንዲሁም የሠመራ ዮኒቨርሲቲን አመሥግነዋል። የሠመራ ዩኒቨርሲቲ ኘሬዝዳንት ዶክተር መሐመድ ኡስማን በበኩላቸው ይህ ዕለት ለተከታታይ ጊዜያት የተደረጉ ጥረቶችን በተጨባጭ ያየንበት እና ምርታማ የሆንበት በመሆኑ የህንድ መንግስት ሊመሠገን ይገባዋል ብለዋል። 400 የአካል ጉዳተኞች ተጠቃሚ ለማድረግ ክልል ደረጃ መጥተው ልምዳቸውን ዕውቀታቸውንና ሰብአዊ አገልግሎት በመለገሳቸው አመሥግነዋል።   ይህ ኘሮጀክት የሰብአዊነት ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው በዚህ መሠረት በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ በኩል አፋርን ተደራሽ ማድረግ ምርጫ መሆኑን ጠቅሰው ይህ ጅማሬ እንጂ መጨረሻ እንዳልሆነ አያይዘው አምባሳደሩ ተናግረዋል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካይ የሆኑት አቶ አሳልፈው አህመዲን ይህ ኘሮግራም ለተከታታይ ሁለት ወራት የሚቆይ መሆኑን ገልፀዋል። የአካል ድጋፍ መሠረታዊ ፍላጎት በመሆኑ ይህን በማሟላት የዜጎቹን አምራችነት ተሳትፎ መጨመር ማሳደግ እንደሚገባ እስረድተዋል። በአሁኑ ዘመቻ የሚሰጠው ሰው ሰራሽ የአካል ድጋፉ የ10 ሚሊዮን ብር ግምት እንዳለውም ተናግረዋል። የክልሉ ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ቢሮ ኀላፊ ወይዘሮ ፋጡማ መሐመድ በበኩላቸው የክልሉ ነዋሪዎች ይሄን ዕድል ለማግኘት በተለያዩ አጎራባች ክልሎች ሲሄዱ እንደ ነበር ተናግረዋል። ዛሬ ላይ ክልሉ ድረስ መጥተው አገልግሎቱ እንዲሰጥ ያደረጉትን የህንድ መንግስት፣የፌዴራል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ሚኒስቴርና የሠመራ ዩኒቨርሲቲን አመስግነዋል።
የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚና የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር በጋራ ለመሥራት ተስማሙ
Apr 26, 2024 61
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡-የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚና የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር በጋራ ለመሥራት ተስማሙ። የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚና የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር በተለያዩ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመሥራት የሚያስችል ስምምነት ተፈራርመዋል። የመግባቢያ ስምምነቱን የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዚዳንት አቶ ዛዲግ አብርሃ እና የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ ተፈራርመዋል። የሁለቱ ተቋማት ስምምነት የአመራር ልማት ፕሮግራም፣ የአመራር እውቅና አሰጣጥ ሥርዓትና የሀሳብ ማመንጫ ማዕከል ማቋቋምን የሚያካትት መሆኑ ተጠቅሷል። ስምምነቱ ከተሞችን የሚመሩ አመራሮችን ክህሎት ለማጎልበትና በአመራር አቅም ግንባታ ስርዓት ላይ ሰፊ ስራ ለመስራት የሚያስችል ነው ተብሏል።። እንዲሁም በከተማ ልማት ላይ የተሻሉ ሥራዎችን ለሠሩ አመራሮች እውቅናና ሽልማት መስጠትን ያካተተ መሆኑ ተጠቅሷል። በተጨማሪ በከተማ ልማት ላይ በጥናት ላይ የተመሰረቱ የተሻሉ ሀሳቦችን ለማቅረብ የሚያስችል የሀሳብ ማመንጫ ማዕከል ማቋቋምን እንደሚያካትት ተገልጿል።  
በአገልግሎት አሰጣጥ  ሂደት የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍና  የተጠያቂነት አሰራርን መዘርጋቱን  የሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ገለጸ 
Apr 25, 2024 98
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 17/2016 (ኢዜአ)፦ በአገልግሎት አሰጣጥ ሂደት የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍና የተጠያቂነት አሰራርን መዘርጋቱን የሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ገለጸ ። ኤጄንሲው የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈጻጽም ሪፖርቱን ከተጠሪ ተቋማት ጋር ገምግሟል። የኤጀንሲው የዕቅድና በጀት ዳይሬክተር አቶ ጥጋቡ ሹምዬ እንዳሉት፤ ኤጀንሲው በሁሉም ጽህፈት ቤቶቹ የወሳኝ ኩነትና የነዋሪነት ምዝገባ ተልዕኮውን ወቅቱን ጠብቆ በማከናወን አበረታች ውጤት አስመዝግቧል። ከጤና፣ ከሃይማኖት፣ ከትምህርት፣ ከዕድሮች እና ከሌሎች ተቋማት ጋር የተጀመሩ ቅንጅታዊ ስራዎችም ለኤጀንሲው ወቅታዊ ምዝገባ ስርዓት መሳለጥ እንዳገዙ አብራርተዋል። በወቅታዊ ምዝገባ ረገድ በዘጠኝ ወራት ውስጥ የዕቅዱን 91 በመቶ በላይ በማሳካት ከባለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ከ24 በመቶ በላይ እምርታ ማምጣቱን ጠቁመዋል። በነዋሪዎች መታወቂያ አገልግሎት አሰጣጥ ረገድም ከ93 በመቶ በላይ ዲጂታል መታወቂያ ተደራሽ ማድረጉን ጠቅሰው፤ ጤናና መሰል ችግሮች ላሉባቸው ነዋሪዎች የቤት ለቤት አገልግሎት መስጠቱን አንስተዋል። ኤጀንሲው ዘመናዊና ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት የሚያስችለውን በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር በመዘርጋት ከአንድ ነጥብ ስድስት ሚሊዬን በላይ ዜጎች አገልግሎት እንዲያገኙ ማስቻሉንም ተናግረዋል። በአገልግሎት ሂደት የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ የተጠያቂነት አሰራር ዘርግቶ ገቢራዊ ማድረጉን ጠቅሰዋል።   የሲቪል ምዝገባና ነዋሪነት አገልግሎት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ዮናስ አለማየሁ በበኩላቸው ኤጀንሲው ከማዕከል እስከ ወረዳ ባለው መዋቅር የሪፎርም ስራዎችን በመተግበር አገልግሎቱን ለማሻሻል እየሰራ ነው። በሪፎርሙም የተቋሙን አገልግሎቶች ከዕጅ ንኪኪ ነጻ በሆነ ቴክኖሎጂ ስርዓት በማስገባት ትኩረት መሰጠቱን ገልጸው፤ በሁሉም ዘርፎች አበረታች ስኬቶች እንደተመዘገቡ አንስተዋል። ያም ሆኖ ኤጀንሲው ተገልጋዮችን በሚፈለገው ልክ ማርካት ባለመቻሉ የሪፎርም አሰራር ስርዓቶች ትግበራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። በተለይም ለኤጀንሲው ቁልፍ የመልካም አስተዳደር ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ተጠያቂነትን መሰረት ያደረጉ እርምጃዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ነው ያነሱት።          
በስነ-ተዋልዶ የጤና ችግሮች ምክንያት በአፍላ ወጣቶች ላይ የሚከሰተውን ሞትና ጉዳት መቀነስ ትኩረት ተሰጥቷል
Apr 25, 2024 130
ጂንካ፤ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፦ በስነ-ተዋልዶ የጤና ችግሮች ምክንያት በአፍላ ወጣቶች ላይ የሚከሰተውን ሞትና ጉዳት የመቀነስ ተግባር ትኩረት መሰጠቱን የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ በደቡብ ኢትዮጵያ፣ አማራ፣ ኦሮሚያ፣ ሶማሌና ጋምቤላ ክልሎች በቀጣይ ሶስት አመታት የሚተገበር በአፍላ ወጣቶችና በወጣቶች የጤና አገልግሎት ላይ ያተኮረ ፕሮጀክት የማብሰሪያ ፕሮግራም ዛሬ በጂንካ ከተማ አካሂዷል። በአፍላ ወጣቶችና በወጣቶች የጤና አገልግሎት ላይ ያተኮረ ፕሮጀክቱ በፓዝ ፋይንደር ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ ይፋ የተደረገ ሲሆን ለትግበራ ከ192 ሚሊዮን ብር በጀት በላይ መመደቡ ታውቋል። በጤና ሚኒስቴር ከፍተኛ የፕሮጀክት ግራንት አስተዳደር አማካሪ አቶ ውቤ ደምሴ እንደገለጹት የአፍላ ወጣቶች ጤና ጉዳይ በልዩ ትኩረት የሚሰራ ነው።   የጤና ሚኒስቴር የወጣቶችንና የአፍላ ወጣቶችን ጤና ለማስጠበቅና ተጋላጭነታቸውን ለመቀነስ ትኩረት መስጠቱን ተናግረዋል። በአምስት አመቱ ስትራቴጂክ ዕቅድ እንዲሁም በሶስት አመቱ የኢንቨስትመንት ፕላን ውስጥ በማካተት እየሰራ እንደሚገኝ አንስተዋል። ለዚህም የጤና አገልግሎቶች ማሻሻልና ምቹ ማድረግ የሚጠበቅ ሲሆን በ2025 ደግሞ 80 በመቶ የሚሆነው የጤና ተቋማትና ባለሙያዎች አቅም በማጎልበት የአፍላ ወጣቶች የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ደረጃውን የጠበቀና ምቹ እንዲሆን እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም አሁን ላይ 13 በመቶ ላይ ያለውን አላስፈላጊ የአፍላ ወጣቶች እርግዝና እኤአ በ2030 ወደ 6 ነጥብ 5 በመቶ ለማውረድ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከዚህ በተጨማሪ ወጣቶች ስለ ስነ-ተዋልዶና የጤና ችግሮች በቂ መረጃ የሚያገኙበት ''የኔ ታብ''የተሰኘ የበይነ-መረብ መተግበሪያ አገልግሎት እንዲሰጥ መደረጉን አንስተዋል። ዛሬ የተበሰረው ፕሮጀክትም እንደ ሀገር የአፍላ ወጣቶችና የወጣቶችን ጤና ለማጎልበትና ከውስብስብ ችግሮች ለመታደግ መንግስት ለሚሰራቸው ስራዎች አጋዥ መሆኑን ገልፀዋል። በስነ- ተዋልዶና በተያያዥ ችግሮች በአፍላ ወጣቶች ላይ የሚከሰተውን ሞት ለመታደግ በቅንጅት ሊሰራ እንደሚገባ ተናግረዋል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ነብዩ ቤዛ ፤ ወጣቶች በአዕምሮ፣ በአካልና በማህበራዊ እድገት የሚያሳዩት ለውጥ ለሀገራዊ እድገት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። "ወጣቶችን ለውስብስብ የጤና ችግሮች እያጋለጡ ያሉ አደንፃዥ ዕፆች፣ በፆታዊ ግንኙነት ወቅት የሚፈጠሩ ያልተፈለገ እርግዝና፣ አባላዘር፣ኤች አይ ቪ አዲስና ለመሰል ተላላፊ በሽታዎች ተጋላጭነታቸውን ለመቀነስ በቅንጅት ይሰራል" ብለዋል ። ዛሬ የተጀመረው ፕሮጀክትም የክልሉ ጤና ቢሮ በወጣቶችና በአፍላ ወጣቶች ስነ-ተዋልዶና ጤና ላይ ለሚሰራቸው የጤና ልማት ስራዎች አጋዥ መሆኑን አስታውቀዋል።      
በዘጠኝ ወራት ውስጥ ከ132 ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያላቸው ጥራታቸውን ያልጠበቁ መድሀኒቶች ተወግደዋል
Apr 25, 2024 104
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ132 ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያላቸው ጥራታቸውን ያልጠበቁ መድሀኒቶች ወደ ሀገር እንዳይገቡ እንዲሁም እንዲወገዱ ማድረጉን የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን አስታወቀ። የባለስልጣኑ የመድሃኒት ዘርፍ ምክትል ዳሬክተር አቶ ስዩም ወልዴ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለስልጣኑ የመድሃኒት ጥራት፣ ደህንነትና ፈዋሽነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ስትራቴጂክ ዕቅዶች አውጥቶ እየሰራ ነው። በዚህም ከመግባቢያና መውጫ ኬላዎች ጀምሮ በመድሃኒት ዘርፍ አምራቾች፣ አስመጪና ላኪዎች ላይ ጠንካራ የቁጥጥር እና ክትትል ስራዎችን ማከናወን መቻሉን አንስተዋል። ባለስልጣኑ በዘጠኝ ወራት ውስጥ ባደረገው ቁጥጥርና ፍተሻ 61 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር የሚገመቱ መድሃኒቶችን ጥራትና ፈዋሽነት በማረጋገጥ ወደ አገር ውስጥ እንዲገቡ ማድረጉን ጠቅሰዋል። ነገር ግን 132 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያላቸው መድሀኒቶች ጥራት፣ ደህንነትና ፈዋሽነታቸው ባለመረጋገጡ ወደ ሀገር እንዳይገቡ እና እንዲወገዱ መደረጋቸውን ተናግረዋል። በዘጠኝ ወራት ውስጥ ለ291 የአገር ውስጥ አስመጪና አከፋፋይ ተቋማት ፍቃድ መሰጠቱን ጠቁመዋል። ፈቃድ የተሰጣቸው መድሃኒት አምራቾች ወደ ስራ ከመግባታቸው በፊትም ሆነ በኋላ ጥብቅ ቁጥጥርና ፍተሻ እንደሚደረግ ገልጸው፤ በበጀት ዓመቱ 773 ናሙና ተወስዶ ፍተሻ ስለመደረጉ ለአብነት ጠቅሰዋል።        
በወገራ ወረዳ በእንቃሽ እና አካባቢው በሕገወጥ መንገድ ሲንቀሳቀሱ የቆዩ ታጣቂዎች የሰላም አማራጭን ተቀበሉ
Apr 25, 2024 79
ባሕር ዳር፤ ሚያዝያ 17/2016 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በወገራ ወረዳ በእንቃሽ እና አካባቢው ታጥቀው ሲንቀሳቀሱ የነበሩ 14 ታጣቂዎች የሰላም አማራጩን ተቀብለው ወደ ሕዝብ እና መንግሥት ተመልሰዋል። የሰላም አማራጩን ተቀብለው የተቀላቀሉ ታጣቂዎችም ለሰላም ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። ታጣቂዎቹ መንግሥት ላደረገላቸው ይቅርታ አመሥግነው በቀጣይ ወደ መደበኛ ሕይወታቸው ተመልሰው የአካባቢያቸውን ሰላም እና ልማት ለማረጋገጥ እንደሚሠሩም ተናግረዋል።   በወረዳው ዘላቂ ሰላምን ለማምጣት ከሀገር መከላከያ ሠራዊት፣ ከሃይማኖት አባቶች፣ ከሀገር ሽማግሌዎች እና ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ እየተሠራ እንደሚገኝም የወገራ ወረዳ ዋና አሥተዳዳሪ ይናገር ወረታው ተናግረዋል። ዋና አሥተዳዳሪው ፀረ ሰላም እና ፀረ ልማት አጀንዳ በማራገብ ኅብረተሰቡን ለእኩይ ድርጊት የሚያነሳሱ ግለሰቦችን መታገል አስፈላጊ መሆኑን መናገራቸውን አሚኮ ዘግቧል። ለዚህ ደግሞ ከፀጥታ መዋቅሩ ጋር እጅ እና ጓንት ሆኖ በመሥራት ለዘላቂ ሰላም መትጋት እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት። የሚፈጠሩ ችግሮችን በሠለጠነ መንገድ በውይይት ለመፍታት መሞከር ተገቢ መሆኑን ኀላፊው አንስተዋል፡፡ ሰላምን ማረጋገጥ የሁሉም ድርሻ በመሆኑ ሁሉም የሚጠበቅበትን ሃላፊነት በአግባቡ መወጣት እንደሚገባው ዋና አሥተዳዳሪው መናገራቸውን የዞን ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች መምሪያ መረጃ ያመላክታል።
ለመጪው የትንሣኤ በዓል መሰረታዊ የምግብ ፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ ዝግጅት ተደርጓል - የአዲስ አበባ ህብረት ሥራ ኮሚሽን
Apr 25, 2024 130
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- ለመጪው የትንሣኤ በዓል መሰረታዊ የምግብ ፍጆታ ምርቶችን በበቂ ሁኔታ እና በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ ዝግጅት መደረጉን የአዲስ አበባ ህብረት ሥራ ኮሚሽን አስታወቀ። ኮሚሽኑ የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይፈጠር 1 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር የሚገመት የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በሸማች ማኅበራት በኩል እንደሚያቀርብ ነው የገለጸው። የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር ሀብተየስ ዲሮ እንደገለጹት ለትንሣኤ በዓል የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይከሰት ከክፍለ ከተማ እስከ ወረዳ ግብረ ኃይል ተዋቅሮ ሥራ ጀምሯል። በዚህም ጤፍ፣ ዱቄት፣ የቁም እንስሳት፣ እንቁላል፣ ሽንኩርትና ሌሎች ምርቶች በዩኒየኖች አማካኝነት ወደ ሸማች ኅብረት ሥራ ማኅበራት እየገቡ መሆኑን ተናግረዋል። ምርቶቹ በ800 የሸማቾች ሱቆችና በ137 የእሁድ ገበያዎች ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እንደሚቀርቡም ገልጸዋል። በሸማቾች ማህበራት ስር የሚገኙ 246 ስጋ ቤቶችም በኪሎ ከ400 እስከ 460 ብር እና በቅርጫ ሥጋን ለማቅረብም ዝግጅት ማድርጋቸውን ነው ምክትል ኮሚሽነሩ የተናገሩት።   በኮሚሽኑ የሬጉላቶሪ ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር ተጫነ አዱኛ በበኩላቸው፥ ለበዓሉ የሚቀርቡ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ለኅብረተሰቡ በትክክል እንዲደርሱ ጠንካራ ቁጥጥር እንደሚደረግ አመልክተዋል።  
ባለፉት ዘጠኝ ወራት በወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ18 ቢሊየን ብር በላይ የሚገመት የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ተከናውኗል
Apr 25, 2024 76
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡-ባለፉት ዘጠኝ ወራት በወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ18 ቢሊየን ብር በላይ የሚገመት የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎቶች ማከናወን መቻሉን የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የተቋሙን የ2016 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አቅርቧል። ሚኒስትሯ ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ ከመላ ኢትዮጵያ የተውጣጡ ከ24 ሚሊየን በላይ ወጣቶች ተሳትፈዋል። የበጎ ፈቃድ ሥራዎቹ አረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር፣ የአቅመ ደካሞችን ቤት ማደስ፣ ደም ልገሳ፣ የመንገድ ደኅንነት አገልግሎት፣ ሰብዓዊ ድጋፎችን ጨምሮ በ13 የስምሪት መስኮች የተከናወኑ መሆኑንም አመልክተዋል። በወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎትም ወጣቶቹ ወደ ተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች ተዘዋውረው አገልግሎት መስጠታቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም የበጎ ፈቃደኝነት ግንዛቤና አስተሳሰብን ማዳበራቸውንና የሕዝቡን ማኅበራዊ ትስስር ማሳደጋቸውን ገልፀዋል። አገልግሎቱ ወጣቶች የሌሎችን ባህል፣ እሴትና ልምድ እንዲቀስሙ ዕድል የፈጠረ መሆኑንም ነው ያብራሩት። ወጣቶቹ በሰጡት ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ18 ቢሊየን ብር በላይ የሚገመት የልማትና የማኅበራዊ አገልግሎቶች መከናወናቸውንም ነው ሚኒስትሯ ያብራሩት። በወጣቶች ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ58 ሚሊየን በላይ የኅብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ መሆናቸውን አብራርተዋል። የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ940 ሺህ በላይ ወጣቶችን በሰላም ግንባታና ግጭት መከላከል ሥራ ላይ ማሳተፉም ተገልጿል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም