ማህበራዊ
የመስቀል ደመራ በዓል ያስገኘውን የአንድነትና የፍቅር እሴቶች በመጠቀም ለዘላቂ ሰላምና እድገታችን ልንተጋ ይገባል--ብፁዕ አቡነ ገሪማ
Sep 27, 2023 62
ዲላ ፤ መስከረም 16 /2016(ኢዜአ)፡- የመስቀል ደመራ በዓል ያስገኘውን የአንድነትና የፍቅር እሴቶች በመጠቀም ለዘላቂ ሰላምና እድገታችን ልንተጋ ይገባል ሲሉ የጌዴኦ፣ አማሮ ቡርጂ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገሪማ ተናገሩ። የመስቀል ደመራ በዓል በጌዴኦ ዞን ዲላ ከተማ ሁለገብ ስታዲዬም በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስርዓቶች በድምቀት ተከብሯል። በበዓሉ የእምነቱ አባቶች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች፣ ዲያቆናትና ምእመናን የተገኙ ሲሆን በያሬዳዊ ዜማ፣ በስብከተ ወንጌልና በተለያዩ ሃይማኖታዊ ክንዋኔዎች ተከብሯል። በበዓሉ የታደሙት የጌዴኦ፣ አማሮ ቡርጂ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገሪማ እንዳሉት የመስቀል በዓል ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ያለውን ፍቅር ያሳየበት ነው። እኛም ከክርስቶስ ፍቅር በመማር ለወገኖቻችን ፍቅርን፣ ትህትናን እና አንድነትን ማሳየት አለብን ብለዋል። በተለይም የደመራ በዓል በጋራ ከሆንን ጥንካሬን እንዲሁም ብርሃናችን ጨለማን የሚገልጥ መሆኑን እንደሚያስተምር አስረድተዋል ። በመሆኑም የመስቀል ደመራ ያስገኘልንን የአንድነት እሴቶች በመጠቀም ለዘላቂ ሰላማችንና እድገታችን ልንተጋ ይገባል ስሉ ተናግረዋል። እንዲሁም በዓሉን ሲከበር የተቸገሩ ወገኖቻችን በመጠየቅና በመደገፍ ሊሆን እንደሚገባ አመላክተዋል። የመስቀል ደመራ በዓል ከሃይማኖታዊ ይዘቱ በተጓዳኝ የኢትዮጵያ መገለጫ የሆነ የዓለም ቅርስ ነው ያሉት ደግሞ የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዶክተር ዝናቡ ወልዴ ናቸው። በዓሉን መንከባከብ ብሎም ጠብቆ ለትውልድ ማሸጋገር የሁሉም ሃላፊነት መሆን ጠቅሰው "በተለይ ከደመራ እሴቶች በመማር ለሀገር ሰላምና ብልፅግና በጋራ መቆም አለብን" ብለዋል። በተለይ የሚያለያዩንን ነገሮች በውይይት በመፍታት የበለጸገች ሀገር ለትውልድ ማውረስ አለብን ሲሉ አስገንዝበዋል። የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዳንኤል ሽፈራው በበኩላቸው ደመራ በርካታ ችቦዎችን በአንድ ያስተሳሰረ የመደመር ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑንም ከመስቀል ደመራ ያገኘነውን የሰላምና የአንድነት እሴቶችን በመጠቀም ለከተማችን ሰላምና ሁለንተናዊ እድገት ልንጠቀም ይገባል ሲሉ ገልፀዋል። በበዓሉ ላይ የሃይማኖት አባቶችና ምዕመናን እንዲሁም የዞኑ የመንግስት የሥራ ሃላፊዎች ታድመዋል። በተመሳሳይ የመስቀል ደመራ በዓል በአርባ ምንጭ፣ በሆሳዕና፣ በዲላ፣ በሚዛን አማንና ቦንጋ ከተሞችም በተለያዩ ሃይማኖታዊ ኩነቶች በደመቀ ሁኔታ ተከብሯል።    
 የደመራ በዓል በሰላም እንዲጠናቀቅ ወጣቶች ያበረከቱት  አስተዋጽኦ አርያነት ያለው ነው-የባህር ዳር  ሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅ 
Sep 27, 2023 59
ባህር ዳር ፤ መስከረም 16 /2016 (ኢዜአ)፡- የመስቀል ደመራ በዓል በሰላም ተከብሮ እንዲጠናቀቅ ወጣቶች ያበረከቱት አስተዋጽኦ አርያነት ያለውና ሃላፊነት ከሚሰማው ትውልድ የሚጠበቅ ነው ሲሉ የባህር ዳር ሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅ መላከ ሰላም ኤፍሬም ሙሉዓለም ገለጹ። የደመራ በዓል በባህር ዳር ከተማ የሃይማኖት አባቶችና የከተማዋ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት በድምቀት ተከብሮ በሰላም መጠናቀቁን የከተማው አስተዳደር አስታውቋል። የባህር ዳር ሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅ መላከ ሰላም ኤፍሬም ሙሉዓለም በወቅቱ እንደገለጹት፤ የደመራ በዓል ተቀብሮ የነበረውን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ለማውጣት ስራ የተጀመረበት የሰላም ሥነ-ሥርዓት ነው። ይህ በየዓመቱ በድምቀት የሚከበረው የመስቀል ደመራ በዓል በሰላም እንዲከበር ወጣቱ ሃላፊነት እየወሰደ ሃይማኖታዊ ግዴታውን እየተወጣ ይገኛል ብለዋል። ይህ ተግባር ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ጠቅሰው፤ የባህር ዳር ከተማ ወጣቶች ያበረከቱት አስተዋጽኦ ከፍ ያለ ምስጋና እንደሚገባቸው አስታውቀዋል። ''የመስቀል በዓል ለክርስትና እምነት ተከታዮች ሃይማኖታዊ በዓል ቢሆንም በዩኒስኮ የተመዘገበ የሀገር ሃብት ጭምር ነው'' ያሉት ደግሞ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ አስሜ ብርሌ ናቸው። በከተማዋ ለሚከበሩ በርካታ ሃይማኖታዊና ባህላዊ በዓላት በሰላም መጠናቀቅ የከተማዋ ነዋሪዎች በተለይም የወጣቶች ዓርያነት ያለው ተግባር ምስጋና ይገባቸዋል ብለዋል። በባህርዳር በተከበረው የመስቀል ደመራ በዓል ላይ በርካታ የከተማዋ ነዋሪዎች፣ የአድባራትና የገዳማት አስተዳዳሪዎች እንዲሁም የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ተገኝተዋል።  
ህዝቡ የመስቀል በዓልን ሲያከብር አብሮነቱን በማጠናከር ሊሆን ይገባል- ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል
Sep 27, 2023 56
ጋምቤላ ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፡- ህዝቡ የመስቀል በዓልን ሲያከብር አንድነቱንና አብሮነቱን በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የጋምቤላ፣ የአሶሳ፣ የቄለም ወለጋና የደቡብ ሱዳን አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል ገለጹ። የመስቀል ደመራ በዓል በጋምቤላ በድምቀት ተከብሯል። ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል በክብረ በዓሉ ላይ፤ ምዕመኑ የአንድነትና የአብሮነት እሴት በማጠናከርና የተቸገሩ ወገኖችን በመደገፍ በዓሉን ማክበር እንዳለበት አመልክተዋል። የመስቀል ደመራ በዓል የፍቅር፣ የአንድነት፣ የነፃነትና የትብብር እሴት መገለጫ ዋነኛ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ምዕመኑ በዓሉን ሲያከብር ይህኑ ታሳቢ ባደረገ መልኩ ሊሆን እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የጋምቤላ ክልል ህዝብ ባለፉት ዓመታት አንድነቱንና አብሮነቱን በማጠናከር ሰላሙን በመጠበቅ ረገድ ያሳየውን ቁርጠኝነት በቀጣይም አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል። ምዕመኑ በማህበራዊ የትስስር ገፆች ጥላቻን በመስበክ ሀገርን ለማፍረስ እየተደረገ ባለው እኩይ ተግባር ሳይታለል ለክልሉ ብሎም ለሀገሩ ሰላምና ልማት በትጋት ሊሰራ እንደሚገባ መልዕክት አስተላልፈዋል። የጋምቤላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ አቶ ሳይመን ቲያች በክብረ በዓሉ ላይ እንደገለጹት፤ የመስቀል ደመራ በዓል ከሃይማኖታዊ ትውፊቱ ባለፈ የቱሪስት መስህብ በመሆን ፋይዳው የጎላ ነው ብለዋል። የመስቀል ደመራ በዓል ለቱሪዝም ኢንዱስትሪው እድገት እንዲውል ለሚደረገው ጥረት የከተማው አስተዳደር ያልተቆጠበ ድጋፍ እንደሚሰጥ አስታውቀዋል። የመስቀል ደመራ በዓል ኃይማኖታዊና ባህላዊ ትውፊቱን በጠበቀ መልኩ በጋምቤላ ከተማና አካባቢው በርካታ የዕምነቱ ተከታዮች በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል።  
ህዝበ ክርስቲያኑ ሰላምና አብሮነትን አጠናክሮ ማስቀጠል አለበት - ብፁዕ አቡነ እንጦንስ 
Sep 27, 2023 104
ጭሮ/አዳማ ባሌ ሮቤ፤ መስከረም 16 /2016(ኢዜአ)፡- ህዝበ ክርስቲያኑ ሀይማኖታዊ ሥነ-ሥርዓቱን በመጠበቅ ሰላምና አብሮነትን አጠናክሮ ማስቀጠል እንዳለበት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የምዕራብ ሐረርጌና የአፋር ክልል ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ ገለጹ። የመስቀል ደመራ በዓል በጭሮ ፣ በባሌ ሮቤና አዳማ ጨምሮ በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በድምቀት ተከብሯል። በጭሮ ከተማ በተከበረው በዓል ላይ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ ባስተላለፉት መልዕክት በዓሉ ሲከበር በችግር ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን መርዳት፣ መተሳሰብና መከባበርን በማጠናከር ሊሆን እንደሚገባ አሳስበዋል። ህዝበ ክርስቲያኑ ሀይማኖታዊ ሥነ-ሥርዓቱን በመጠበቅ ሰላምና አብሮነትን በተግባር ማሳየቱን አጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል። የጭሮ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ አሳና መሀመድ በበኩላቸው ፤ በደመራ አከባበር ሥነ-ሥርዓት ላይ ህዝቡ የአከባቢውን ሰላም በመጠበቅና የተቸገሩትን በመርዳት ማክበሩ መጪው ጊዜ ብሩህ ተስፋ ይዞ የሚመጣ መሆኑን ያመለክታል ብለዋል። የከተማው ወጣቶች በዓሉ በሰላም እንዲከበር የሀይማኖት ልዩነት ሳይገድባቸው ያሳዩት አንድነት የሚደነቅ መሆኑንም ገልጸዋል። በሌላ በኩል በአዳማ ከተማ በተከበረው የመስቀል ደመራ በዓል ላይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የምስራቅ ሸዋ ዞን ሀገረስብከት ሊቀ ጳጳስ ቡፁ አቡነ ጎርጎሪዮስ፤ ችግሮቻችንና በደላችን የተሻረው በመስቀል ነው ፤ አሁንም በሀገራችን ሰላም እንዲፀና መስራት ይጠበቅብናል ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል። መስቀሉ ጥላቻና የጥል ግድግዳን ያፈረሰ፤ ሰላም ፣አብሮነት፣ መቻቻልና አንድነትን ያጎናፀፈን በመሆኑ ከጥላቻና መገፋፋት በመራቅ አንድነትና ፍቅር እንዲያብብ መስራት ይኖርብናል ሲሉም ገልጸዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ምክትል ክንቲባ አቶ ሙላቱ ዲባ ፤ በበዓሉ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ የመስቀል በዓል ሁሉን በእኩልነት የምስተናገደበት ነው፤ ከመስቀሉ ተምረን ለሀገራችን ሰላም በአንድነት መቆም አለብን ብለዋል። በዚህም ሁሉም በዓሉን ከማክበር ባለፈ የከተማውንና የአካባቢውን ሰላም በመጠበቅ ለሀገር ሰላም በጋራ መቆም እንደሚገባ አመልክተዋል። በዓሉ በተመሳሳይ በባሌ ሮቤ ከተማ የሃይማኖት አባቶች፣ የዕምነቱ ተከታዮችና ሌሎችም እንግደች በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል። በበዓሉ አከባበር ሥነ ሥርዓት ላይ ካህናትና የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የተለያዩ ዝማሬዎችን አቅርበዋል። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሮቤና አካባቢዋ ሃገረ ስብከት ፀሐፊ ቄስ ያሬድ ገብረማሪያም ባስተላለፉት መልዕክት፤ መስቀል የአብሮነት በዓል መሆኑን ገልጸዋል። የደመራ በዓል ራሰን መስጠትን የሚጠይቅ በመሆኑ በተለይ ወጣቱ ትውልድ ፈተናዎችን በመቋቋም ሀገሩን ማሻገር እንዳለበት አመልክተዋል፡፡ በመርሃ ግብሩ ላይ የሮቤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ንጋቱ ሞቱማን ጨምሮ ሌሎችም አመራሮችና የእምነቱ ተከታዮች ተገኝተዋል።    
ሕብረተሰቡ የመስቀል በዓልን ሲያከብር በችግር ላይ የሚገኙ ወጎኖችን በመደገፍ ሊሆን ይገባል - የሃይማኖት አባቶች
Sep 27, 2023 93
አዲስ አበባ፤ መስከረም 16/2016(ኢዜአ)፦ ሕብረተሰቡ የመስቀል በዓልን ሲያከብር በችግር ላይ የሚገኙ ወጎኖችን በመደገፍ ሊሆን እንደሚገባ ኢዜአ ያነጋገራቸው የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት አባቶች አሳሰቡ። የመስቀል በዓል ከሃይማኖታዊ እሴቱ በተጨማሪ አብሮነትንና የእርስ በርስ መደጋጋፍ የሚገለጽበት መሆኑንም ነው የተናገሩት፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል መምሪያ መምህር አባ አፈወርቅ ዮሐንስ፣ የመስቀል በዓል ስናከብር በችግር ውስጥ ለሚገኙ ወገኖች ማዕድ በማጋራት ሊሆን ይገባል ብለዋል። ከተረፈን ብቻ ሳይሆን ካለን ለወገኖቻቸን ማካፈል አለብን ነው ያሉት፡፡ በሸገር ከተማ አስተዳደር የዱከም ቅዱስ ገብርዔል ቤተክርስቲያን አስተዳደሪ መጋቢ ሃይማኖት ቆሞስ አባ ገብረ ማሪያም ገብረ መድን በበኩላቸው፣ በዓላትን ከተቸገሩ ወገኖች ጋር ማክበር ኢትዮጵያዊ እሴት ነው ብለዋል፡፡ የተቸገሩትን በመርዳት የኢትዮጵያዊያን መገለጫ የሆነውን የመደጋገፍ ባህል ማጎልበት እንደሚገባ አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የቋሚና ጊዜያዊ ፕሮጀክቶች መምሪያ ኃላፊ መልዕከ ሕይወት ቆሞስ አባ ወልደየሱስ ሰይፈ ምዕመኑ ከበዓላት ባሻገር በጎነት ባህል እንዲሆን የበኩሉን ሚና ሊወጣ ይገባል ነው ያሉት፡፡   ከዚህ አኳያ የፍቅርና የአብሮነት ምሳሌ የሆነውን የመስቀል በዓል እርስ በርስ በመደጋገፍ ልናከብር ይገባል ነው ያሉት፡፡ የመስቀል በዓል የሰላም፣የፍቅርና የአንድነት በዓል እንዲሆን የሃይማኖት አባቶቹ መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።  
የመስቀል ደመራ በዓል በሐረር፣ በጋምቤላ፣ በአሶሳ እና በድሬደዋ ከተሞች እየተከበረ ነው
Sep 27, 2023 96
ሐረር፣ አሶሳ እና ድሬዳዋ ፤ መስከረም 16/2016(ኢዜአ)፡- የመስቀል ደመራ በዓል በሐረር፣ በጋምቤላ፣ በአሶሳ እና በድሬደዋ ከተሞች በተለያዩ ሃይማኖታዊ ሥርአቶች እየተከበረ ነው። በዓሉን በሰላም፣ በፍቅርና በአብሮነት ከማክበር ባለፈ በመስቀሉ የተገኘውን ሰላምና እርቅ እያሰቡ የተቸገሩትን በመርዳት ማክበር እንደሚገባም የሃይማኖት አባቶች አስገንዝበዋል። የደመራ በዓል በሐረር ከተማ መሃል አደባባይ በታላቅ ሀይማኖታዊ ስነ ስርአት እየተከበረ ሲሆን በበዓሉ ላይ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ የሐረር ከተማና በአካባቢው የሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ታድመዋል።   በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን የምስራቅ ሐረርጌ ሃገረ ስብከት ሊቀ-ጳጳስ አቡነ ኒቆዲሞስ፣ ካህናትና ዲያቆናት፣ መዘምራን እንዲሁም ህዝበ ክርስቲያኑ በበዓሉ ላይ ታድመዋል። ለበዓሉ ድምቀት ካህናትና የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የተለያዩ ያሬዳዊ ዜማ፣ ሽብሸባና ቅኔ እንዲሁም መዝሙሮችን አቅርበዋል። የሃይማኖት አባቶች ባስተላለፉት መልዕክትም በዓሉን በሰላም፣ በፍቅርና በአብሮነት ማክበር እንደሚገባ ገልጸዋል። በአሶሳ ከተማም በዓሉ በርካታ የእምነቱ ተከታዮችና የሃይማኖት አባቶች በተገኙበት በዝማሬ፣ በስብከተ ወንጌል በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስርአቶች እየተከበረ ነው።   በበዓሉ ላይ ንግግር ያደረጉት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የአሶሳ ሃገረ ስብከት ስራ አስኪያጅ አምላከፀሐይ አባ አለምነው ፀጋው እንዳሉት፣ በመስቀል ክርስቶስ የጥል ግድግዳ የፈረሰበት በመሆኑ በልዩ ሁኔታ ይከበራል። "በመስቀሉ የተገኘው እርቅ እና ሠላም በሁላችን ልብ ሊኖር ይገባል ብለዋል" ሥራ አስኪያጁ። "ፈልጉ ይሰጣችኋል" የሚለውን ቅዱስ ቃል መሠረት በማድረግ የእምነቱ ተከታዮች ሠላምን አጥብቀን መፈለግ ይገባናል ሲሉ አስገንዝበዋል። የአሶሳ ከተማ አስተዳደር ወክለው የተገኙት አቶ በድሉ አበራ በበኩላቸው በዓሉ ሲከበር አንድ የሚያደርጉ ጉዳዮች በማጎልበትና አለመግባባቶችን በማስወገድ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። የደመራ በዓል በድሬዳዋም በታላቅ ኃይማኖታዊ እሴቶች በደማቀ ስነስርዓት እየተከበረ ነው። በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ የእምነቱ ተከታዮች በዓሉን እያከበሩ ያሉት በድሬዳዋ ምድር ባቡር አደባባይ ተገኝተው ነው። በበዓሉ ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የድሬዳዋ አገረ ስብከትና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ ተገኝተው መልዕክት አስተላልፈዋል።   በእዚህም የመስቀል ደመራ በዓልን የተቸገሩትን በመርዳትና የታመሙትን በመጠየቅ እንዲሁም አንድነትን በሚያጠናክሩ ተግባራት ማክበር እንደሚገባ መልዕክት አስተላልፈዋል። በዓሉ የሰላም፣ የፍቅር እና የብልጽግና እንዲሆን ምኞታቸውን የገለጹት ብፁዕ አቡነ በርተሎሜዎስ፣ አንድነትና የሀገርን ሰላም በዘላቂነት መጠበቅ እንደሚገባም ገልጸዋል። በበዓሉ ላይ በብዙ ሺህ የሚገመቱ የእምነቱ ተከታዮች፣ የቤተክርስቲያን አባቶች፣ ሊቃውንተ- ቤተክርስቲያናት እንዲሁም የሰንበት ትምህርት ቤቶች ዘማሪዎች እየተሳተፉ ነው። በስነስርዓቱ ላይ ዝማሬና ወረብ ከመቅረብ ባለፈ ተቀብሮ የተገኘውን ብርሃነ መስቀል ምንነት፣ ህይወትና ታላቅ የመዳን በረከትን የተመለከቱ መልዕክቶች ተላልፈዋል። ኢትዮጵያዊ በተባበሩት መንግስታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በማይዳሰስ ቅርስነት ካስመዘገበቻቸው ቅርሶች መካከል የመስቀል ደመራ በዓል አንዱ ነው። የመስቀል ደመራ በዓል ከሃይማኖታዊ ትውፊቱ ባለፈ የቱሪስት መስህብ በመሆን ለአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት አወንታዊ ሚና እየተጫወተ ይገኛል።    
መንግስት የመስቀል በዓልን ሃይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶች ለመጠበቅና ለማልማት ለሚከናወኑ ስራዎች አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል- ሚኒስትር ቀጄላ መርዳሳ
Sep 27, 2023 49
አዲስ አበባ፤ መስከረም 16/2016(ኢዜአ)፦መንግስት የመስቀል በዓልን ሃይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶች ለመጠበቅና ለማልማት ለሚከናወኑ ስራዎች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ቀጄላ መርዳሳ ገለጹ። የመስቀል ደመራ በዓል በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስነ-ስርዓቶች በመስቀል አደባባይ በመከበር ላይ ነው።   የባህልና የስፖርት ሚኒስትር አቶ ቀጄላ መርዳሳ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ኢትዮጵያ ካሏት ታላላቅ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ክብረ በዓላት አንዱና ዋንኛው የመስቀል ደመራ በዓል ነው። በዓሉ የተለያዩ መንፈሳዊና ባህላዊ እሴቶች የተጎናጸፈ መሆኑን ጠቅሰው በኢትዮጵያውያን ዘንድ በደመቀ ሁኔታ እንደሚከበር አመልክተዋል። መስቀል በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ሳይንስና ባህል ድርጅት(ዩኔስኮ) ከኢትዮጵያ አልፎ የዓለም ሕዝብ ሃብትና ንብረት ሆኗል ብለዋል። የመስቀል በዓል ፍቅር፣አብሮነት፣መረዳዳት፣አንድነትና ሰላምን የሚያስተምር መሆኑን ያነሱት ሚኒስትሩ የበዓሉን አስተምህሮ በመከተል በፍቅር አንድ ልንሆንና በሰላም አብረን ልንኖር ይገባናል ሲሉ ገልጸዋል። አቶ ቀጄላ የሚያጋጥሙ ፈተናዎችን በትዕግስት፣በንግግርና በይቅርታ በማለፍ ለኢትዮጵያ ሰላምና አንድነት መስራት እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል። መንግስት የመስቀል በዓል ሃይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶች እንዲጠበቁና እንዲለሙ አልፎም ለትውልድ እንዲተላለፉ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ነው አቶ ቀጄላ ያመለከቱት።              
የመስቀል በዓልን ጥላቻና መከፋፈልን በማስወገድ በአንድነትና በፍቅር ልናከብር ይገባል- ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ
Sep 27, 2023 59
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 16/2016(ኢዜአ)፦ የመስቀል በዓልን ጥላቻና መከፋፈልን በማስወገድ በአንድነትና በፍቅር ማክበር እንደሚገባ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ አሳሰቡ። የመስቀል ደመራ በዓል በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስነ ስርዓቶች በመከበር ላይ ይገኛል። በበዓሉ ላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትሪያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስን የበዓል መልዕክት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ እና የባሕር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብረሃም አቅርበዋል። በመልዕክታቸውም መስቀል ድህነትን የሚሰጥ እንዲሁም ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነት የሚሰበክበት እንደሆነ ገልጸዋል። መስቀል በፈጣሪና በሰው ልጆች እርቅ የተፈጠረበት፤ ጥላቻና መከፋፈል የተሸነፈበት መሆኑን አመልክተዋል። ነገረ መስቀሉ የተለያዩትን የሚያሰባስብ እና የተጣሉትን የሚያስታርቅ የሰላምና የእርቅ ተምሳሌት ነው ብለዋል። ምዕመናን የመስቀሉን አስተምህሮ በመከተል የፍቅር ምሳሌ የሆነውን በዓል በአብሮነትና በጋራ ማክበር ይገባል ነው ያሉት ብፁዕነታቸው። የመስቀሉ ምልክት በሆኑት ሰላም፣ ፍቅር፣ መግባባት፣ አንድነትና ይቅርታ መኖር እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል። በክበረ በዓሉ ላይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅና የባህር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብርሃም፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የኒውዮርክና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ቀጄላ መርዳሳ፣የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አመራሮች፣ ዲፕሎማቶችና ሌሎች የማህበረሰብ ክፍሎች ታድመዋል።
ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልፅግናና ህብረ ብሔራዊ አብሮነት መረጋገጥ በአንድነት መነሳትን ከመስቀል ደመራ ልንማር ይገባል- ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Sep 27, 2023 43
አዲስ አበባ፤ መስከረም 16/2016(ኢዜአ)፦ከመስቀል ደመራ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልፅግና እና ህብረ ብሔራዊነት አብሮነት መረጋገጥ በአንድነት መነሳትን መማር እንደሚገባ የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናገሩ። የመስቀል ደመራ በዓል በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስነ-ስርዓቶች በመከበር ላይ ይገኛል። በስነ-ስርዓቱ ላይም የከንቲባ አዳነች አቤቤን የመስቀል ደመራ መልዕክት የአዲስ አበባ የባህል፣ ኪነጥበባትና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ሂሩት ካሳው አቅርበዋል። በመልዕክታቸውም የመስቀል ደመራ በዓል በዩኔስኮ ለተመዘገበበት 10ኛ ዓመት እንኳን አደረሳችሁ ብለዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የመስቀል ደመራ ትውፊትን ጠብቃ ለትውልዱ በማስተላለፏና በዩኔስኮ እንዲመዘገብ ጉልህ ሚና በመጫወቷ ምስጋና አቅርበዋል። መስቀል ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ድህነት ቤዛ የሆነበትና ራሱን አሳልፎ የሰጠበት የፍቅር መገለጫ መሆኑን ተናግረዋል። ንግስት እሌኒ የቆሻሻ ክምርን ንደው መስቀሉን ከተደበቀበት ማውጣታቸው ብዙ ያስተምራል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያንና አዲስ አበባን የብልፅግና ተምሳሌትነት ለማረጋገጥ እየተጋን ነው ያሉት በመልዕክታቸው፤ ለዚህ ስኬት የመለያየትና የግጭት ቆሻሻዎችን ማስወገድን ከመስቀሉ ደመራ መማር አስፈላጊ ነው ብለዋል። በአንድነት በመነሳት ዘመን የማይሽረው ታሪክ መፃፍ እንደሚገባም አስረድተዋል። የመስቀሉና የደመራ ትውፊት በመዋደድና በመትጋት ልንገልፀው ይገባል ያሉት ከንቲባዋ፤ እኛ ኢትዮጵያውያን የባህል የሃይማኖትና የቋንቋ ልዩነታችን ሲደመር ትልቅ አቅም መሆኑን በመገንዘብ እርስ በእርስ መዋደድን ማጠናከር ተገቢ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያውያንን የህብረ-ብሔራዊ አንድነት እውነታ፣ የልማትና እድገት መሻት ጥረትና ውጤታችንን፣ የነፃነታችን ታሪክን ለመደበቅ ጠላቶቻችን የሚከምሩትን ቆሻሻ ለመናድ በአንድነት መነሳት ይገባል ነው ያሉት። ከአባቶቻችን የችግር መፍቻ ጥበብን በመማር በመስቀሉ መገኘት የተገለጠውን ትምህርት በምግባር በመኖር አርአያ መሆንም ከሁሉም እንደሚጠበቅ አንስተዋል። ለዚህም የፍቅርና የመዋደድን እውነት በየዕለቱ በመግለጥ በመቻቻልና በአብሮነት የኢትዮጵያንና የአዲስ አበባን የሰላም የልማትና የፍቅር ደመራን እንደምር ሲሉም ነው መልዕክታቸውን የቋጩት።
የመስቀል ደመራ  በዓል  ተስፋና ፍቅር ፀንቶ እንዲኖር የምንማርበት ነው - ብጹዕ አቡነ ቀሌምጦስ
Sep 27, 2023 64
ደብረ ብርሃን/ ባህር ዳር/ ወልዲያ / ደሴ ፤ መስከረም 16 /2016(ኢዜአ)፡- የመስቀል ደመራ በዓል እምነት፣ ተስፋና ፍቅር በውስጣችን ፀንቶ እንዲኖሩ የምንማርበት ነው ሲሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሰሜን ሸዋ ሃገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ቀሌምጦስ ገለጹ። በዓሉ በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በድምቀት እየተከበረ ይገኛል። በደብረ ብርሃን ከተማ እየተከበረ ባለው በዓል ላይ ብጹዕ አቡነ ቀሌምጦስ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ከቀደምት አበው እንደተማርነው ሃገርን ለመገንባት ፍቅርንና አንድነትን በማብዛት ተስፋን በመሰነቅ በጋራ ፀንቶ በመቆም መሆን አለበት ብለዋል። የደመራ በዓል ስናከብር እምነት፣ ተስፋና ፍቅር በውስጣችን ፀንቶ እንዲኖሩ የምንማርበት ነው፤ ይህንን ታላቅ በዓል ስናከብር ካለን ላይ ለተቸገሩ ወገኖች በማካፈል መሆን አለበት ሲሉ ገልጸዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት በበኩላቸው፤ አካባቢያችንን ነቅተን በመጠበቅና በማልማት ዘላቂ ሰላምን ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል። በደብረ ብርሃን ከተማ የሚስተዋሉ የልማት እድገት ማስቀጠል ሁሉም ሊረባረብ እንደሚገባ አመልክተው፤ አንድነትንና ሰላምን ለማስጠበቅ ከደመራ መማር እንደሚቻል ተናግረዋል። በተመሳሳይ የመስቀል ደመራ በዓል በባህር ዳር ከተማ በርካታ የእምነቱ ተከታዮች በተገኙበት እየተከበረ ይገኛል። በክብረ በዓሉ የባህር ዳር ሀገረ ስብከት ስራ አስኪያጅ መላከ ሰላም ኤፍሬም ሙሉዓለም፣ የባህር ዳር ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ አስሜ ብርሌን ጨምሮ ሌሎች አመራሮች ተገኝተዋል። በአሁኑ ሰዓት በዓሉን አስመልክቶ በሰባኪያን ትምህርት እየተሰጠ ሲሆን በበዓሉ የታደሙት የሃይማኖት አባቶችና የመንግስት የስራ ሃላፊዎች መልዕክት እንደሚያስተላልፉ ይጠበቃል። በወልዲያ ከተማም እንዲሁ የመስቀል ደመራ በዓል በድምቀት እየተከበረ ነው። በስነ-ሰርዓቱ የሰሜን ወሎ ሃገረ-ስብከት ሊቀ-ጳጳስ ብጹዕ አቡነ ኤርሚያስ፣ በርካታ የእምነቱ ተከታዮችና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች የታደሙ ሲሆን ፤ በተመሳሳይ በዓሉ በደሴ ከተማ ሆጤ ስታዲዮም በድምቀት እየተከበረ ይገኛል። በበዓሉ በክልሉ በሚገኙ ሌሎች ከተሞችም እየተከበረ መሆኑ ታውቋል።      
የክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች ለመስቀል በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ
Sep 27, 2023 56
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፦ የክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች ለመስቀል በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ርዕሳነ መስተዳድሮቹ እንዳሉት የመስቀል በዓል የኢትዮጵያዊነት መገለጫ የሆኑ የመተባበር፣ የአብሮነት እና የእርስ በርስ መደጋገፍ እሴቶቻችን በጉልህ የሚንፀባረቁበትና ከዘመን ወደ ዘመን እየተሸጋገረ የመጣ በዓል ነው። የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ እንኳን ለመስቀል በዓል በሰላም አደረሳችሁ ብለዋል፡፡ አቶ ሽመልስ በመልዕክታቸው እንዳሉት የመስቀል በዓል የክረምቱ ጭቃ አልፎ ምድር በአበባ አጊጣ፣ በደመና የተጋረደችው ፀሐይ ፈክታ የሚከበር ውብ በዓል ነው ብለዋል፡፡ የኦሮሞ ህዝብ የመስቀልን በዓል የሚያከብረው በፍቅር፣ በአንድነት፣ በመተሳሰብ እና በይቅርታ ነው፤ መስቀል በኦሮሞ ህዝብ ዘንድ የደስታ በዓል ስለሆነ የዐውደ ዓመት አውራ ተብሎ ይጠራል ብለዋል፡፡ አቶ ሽመልስ መስቀል በሀገራችን የተለያዩት ተገናኝተው፣ የተራራቁት ተቀራርበው፣ ዘመድ ከወዳጅ ተሰባስበው የሚከበር የህብር በዓል ስለሆነ ሁላችንም አብሮነታችንን አጽንተን ልናከብረው ይገባል ነው ያሉት፡፡ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው በእንኳን አደረሳችሁ መልዕክታቸው እንዳሉት የክረምቱ ወራት አልፎ ምድር በብርሃን ጸዳል ስትደምቅ ከአዲስ ዓመት የእንቁጣጣሽ በዓል በኋላ የሚከተለው ህዝቦች በጉጉት የሚጠብቁት የመስቀል በዓል ይከተላል። ይህ በዓል የኢትዮጵያዊነት መገለጫ የሆኑ የመተባበር፣ የአብሮነት እና የእርስ በርስ መደጋገፍ እሴቶቻችን በጉልህ የሚንፀባረቁበት እና ከዘመን ወደ ዘመን እየተሸጋገረ የመጣ በዓል በመሆኑ እርስ በርሳችን በመተጋገዝ እና በፍቅር ማሳለፍ አለብን ብለዋል። የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኡሞድ ኡጁሉ ለደመራና መስቀል በዓላት የእንኳን አደረሳችሁ የመልካም ምኞት መልዕክት አስተላልፈዋል።   ርዕሰ መስተዳድሩ ባስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት፤ የመስቀል በዓል ለረጅም ጊዜ የተራራቁ የቤተሰብ አባላት እና ወዳጅ ዘመዳሞች የሚገናኙበት፣ የተጣሉ የሚታረቁበት፣ የተቸገሩ ወገኖች የሚደገፉበት እና ሌሎች ማኅበራዊ ኩነቶች የሚከወኑበት በዓል ነው ብለዋል። የመስቀል በዓል ሃይማኖታዊ በዓል ቢሆንም ኢትዮጵያዊያን ይህን በዓል የባህላቸው፣ የትውፊታቸው፣ የማኅበራዊ ዕሴቶቻቸው አካል አድርገው እንደሚያከብሩት አስረድተዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ ባስተላለፉት መልዕክት፣ መስቀል የሰላም፣ የአብሮነት፣ የመተሳሰብ፣ የመደጋገፍ፣ የመከባበር እንዲሁም የተጣሉ ይቅር የሚባባሉበት እሴታችን ደምቆ የሚታይበት በዓል ነው ብለዋል፡፡ በዓሉን ስናከብር የሃይማኖቱ አስተምህሮ የሆኑትን አብሮነትን፣ መቻቻልን፣ ፍቅርና መከባበርን በማስፈን ረገድ ለሁሉም አርአያ ሆኖ በመገኘት ሊሆን እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች እንኳን ለመስቀል ደመራ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ሲሉ የመልካም ምኞት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። አቶ ደስታ እንዳሉት መስቀል አምላክ ለሰው ልጅ ያለውን ፍቅሩን የገለፀበት፤ ይቅርታንና የኃጢያት ስርየትን ለሰው ልጆች የሰጠበት መለኮታዊ አንድምታ ያለው ሲሆን በመስቀል ፍቅር፥ ሰላም፥ ይቅርታና መተሳሰብ የሚገለፅበት በመሆኑ በዓሉን ስናከብር የኢትዮጵያዊነታችን ማድመቂያ የእርስ በርስ መዋደዳችን መገለጫ መሆን ይገባል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ዶክተር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ ባስተላለፉት መልዕክት በበዓሉ ወቅት የተቸገሩትን በመርዳት ልናከብር ይገባል ብለዋል። ለዘመናት ተቀብሮ የኖረው የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ከተጫነው ተራራ ከተደበቀበት ስውር ስፍራ ይወጣ ዘንድ በደመራ ሰማያዊ ምልክት የታየበትን ቀን ለምናከብርበት በዓል ለመላዉ የክርስትና እምነት ተከታይ ወገኖቼ እንኳን አደረሳችሁ በማለት ስገልጽ የተሰማኝን ልባዊ ደስታ ከተለየ አክብሮት እና ፍቅር መልዕክት ጋር ነው ሲሉም ጠቅሰዋል፡፡ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልላዊ መንግሥት ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች እንኳን ለመስቀል በዓል አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፏል። በእምነቱ ተከታዮች ዘንድ በአደባባይ ከሚከበሩ ታላላቅ በዓላት አንዱ የሆነው የመስቀል በዓል፣ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት እውነተኛ መስቀሉ ከተቀበረበት መገኘቱ የሚታሰብበት በዓል መሆኑን የገለጸው የክልሉ መንግሥት፣ በኢትዮጵያ በተለዬ ድምቀት የሚከበረው ይህ በዓል በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገበ በመሆኑ የዓለምን ማኅበረሰብ ትኩረት በተለዬ ሁኔታ የሚስብ መሆኑ ተጠቅሷል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለመስቀል በዓል በሠላም አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። በክርስትና ሃይማኖት አማኞች ዘንድ በየዓመቱ መስከረም 16 እና 17 የሚከበረው የደመራና የመስቀል በዓል የአገሪቱን መልካም ገፅታ በማጉላት በኩል ፋይዳው የላቀ ነው ። ይህ በዓል የተስፋ፣ የልምላሜና እንደገና በአዲስ መንፈስ ለስራ የምንነሳሳበት በመሆኑ በዓሉን ስናከብር የሃይማኖቱ አስተምህሮ የሆኑትን አብሮነትን፣ መቻቻልን፣ መከባበርንና ሠላምን ለሁሉም በማስተማርና አርአያ ሆኖ በመገኘት ነው ብለዋል።          
የመስቀል ደመራ በዓል በሀዋሳ እየተከበረ ነው
Sep 27, 2023 44
ሀዋሳ ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን አማኞች ዘንድ በድምቀት የሚከበረው የመስቀል ዋዜማ ደመራ በዓል በሀዋሳ ከተማ እየተከበረ ይገኛል። ከሀዋሳ ከተማ የሃይማኖት አባቶች የዕምነቱ ተከታዮችና ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ የውጭና የሃገር ውስጥ ጎብኚዎች በተገኙበት የደመራ በዓል እየተከበረ ሲሆን ከመስቀል አደባባይ ባሻገር ምእመናንም በየቤተክርስቲያናቱና በቤታቸው ደመራ በመለኮስ ያከብሩታል። በሀዋሳው የደመራ በዓል ሥነ ሥርዓቱ ላይ ጥንግ ድርብ የለበሱ ካህናትና የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች የተለያዩ ዝማሬዎችን እያቀረቡ ይገኛሉ። በደመራው መርሀ-ግብር ላይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሲዳማ ሃገረ ስብከት ዋና ስራ አስኪያጅ መጋቢ ጥበባት ቀሲስ ሞላልኝ መርጊያ እና የአብያተ ክርስቲያናት ካህናትና ምእመናን ተገኝተዋል። የመስቀል ደመራ በዓል ከሃይማኖታዊ ይዘቱ በተጨማሪ ባሉት ባህላዊ ትዕይንቶቹ በዩኔስኮ የማይዳሰስ ቅርስ ሆኖ መመዝገቡ ይታወሳል።            
የመስቀል ደመራ በዓል በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ እየተከበረ ነው
Sep 27, 2023 56
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፦ የመስቀል ደመራ በዓል በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስርዓቶች በመከበር ላይ ይገኛል። በክብረ በዓሉ ላይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ስራ አስኪያጅና የባህር ዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብርሃም፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የኒውዮርክና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ቀጄላ መርዳሳ፣የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አመራሮች፣ ዲፕሎማቶችና ሌሎች የማህበረሰብ ክፍሎች ታድመዋል።   የደመራ በዓል ሃይማኖታዊ ስነ-ስርዓቶች እየተከናወኑ ሲሆን በዓሉን የተመለከቱ ያሬዳዊ ዝማሬዎችም በመቅረብ ላይ ናቸው። የመስቀል ደመራ በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ከሚከበሩ ሃይማኖታዊ በዓላት መካከል አንዱ ነው። በዓሉ እ.አ.አ በ2013 በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) የዓለም ቅርስ ሆኖ መመዝገቡ ይታወሳል።  
የውጭ አገራት ጎብኚዎች በአገር ውስጥ የሚኖራቸው ቆይታ ስኬታማ እንዲሆን በቂ ዝግጅት ተደርጓል - የቱሪዝም ሚኒስቴር
Sep 27, 2023 51
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፦ የውጭ አገራት ጎብኚዎች በኢትዮጵያ የሚኖራቸው ቆይታ ስኬታማ እንዲሆን በቂ ዝግጅት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን የቱሪዝም ሚኒስቴር አስታወቀ። በኢትዮጵያውያን ዘንድ ልዩ ቦታ ከሚሰጣቸው ወራቶች ውስጥ የመስከረም ወር አንዱ መሆኑ ይታወቃል። የዘመን መለወጫ ዕንቁጣጣሽ፣ የመስቀል ደመራ፣ ያሆዴ መስቀላ፣ ዮ ማስቃላ፣ ጊፋታና እሬቻ በመስከረም ወር ብቻ የሚከበሩ በዓላት ናቸው። ይህንንም ተከትሎ የመስከረም ወር በርካታ የውጭ አገራት ጎብኚዎች ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡበት ወር እንደሆነ ይታወቃል። በዓላቱ አብሮነትን በማጠናከርና ሕዝብን በማቀራረብ ረገድ ትልቅ ፋይዳ ያላቸው ሲሆን ጎብኚዎችን በመሳብ ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ እንደሆነ ይታወቃል። ይህንን ወቅት ተከትሎ በዘርፉ ምን አይነት ሥራዎች እየተከናወኑ ነው ሲል ኢዜአ የቱሪዝም ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ታሪኩ ነጋሽን አነጋግሯል። ይህንንም ተከትሎ ሚኒስቴሩ የአገሪቱን ተፈጥሯዊና ታሪካዊ የቱሪዝም መዳረሻዎች ለጎብኚዎች በስፋት ሲያስተዋውቅ መቆየቱን ዳይሬክተሩ ጠቅሰዋል።   በተጓዳኝም፤ የክልል ቱሪዝም ቢሮዎችም መሰል ሥራዎችን መከናወናቸውንም እንዲሁ። ጎን ለጎንም ለበዓላቶቹ ለሚመጡ የውጭ አገራት ጎብኚዎች የቱሪስት መዳረሻዎችን በማስተዋወቅና ቆይታቸውን የሰመረ ለማድረግ ከዘርፉ ተዋንያን ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   ጎብኝዎች ቆይታቸው ስኬታማ እንዲሆን ከአቀባበል ጀምሮ እየተሰራ መሆኑን ገልጸው አስፈላጊ መረጃዎችን የሚያሳውቅ የጎብኚዎች መረጃ ማዕከል ተቋቁሞ ወደ ሥራ መግባቱን ተናግረዋል። ከመሥተንግዶ ጋር በተያያዘ እክል እንዳይገጥማቸው ከሆቴሎችና ከአስጎብኚ ድርጅቶች ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም አመላክተዋል።
 በዓሉን ስናከብር  ለሠላምና ለአብሮነት መጠበቅ  የበኩላችንን ለመወጣት  በመነሳሳት ሊሆን ይገባል- የምክር ቤቱ ዋና ፀሐፊ 
Sep 27, 2023 40
ወልዲያ ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፡- የመውሊድ በዓልን ስናከብር ለአካባቢያችን ብሎም ለሀገራችን ሠላምና አብሮነት መጠበቅ የበኩላችንን ለመወጣት በመነሳሳት ሊሆን ይገባል ሲሉ የሰሜን ወሎ ዞን እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ፀሐፊ ሃጅ አሊጋዝ አስረስ ገለጹ። 1 ሺህ 498ኛው የመውሊድ በዓል በዞኑ ሐብሩ ወረዳ ዳና መስጂድ የእምነቱ ተከታዮች በተገኙበት በደማቅ ስነ-ስርዓት ተከብሯል። የዞኑ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ፀሐፊ በወቅቱ ባስተላለፉት መልዕክት፤ በሀይማኖቱ አስተምሮ መሰረት ህዝቡ ሠላሙንና አብሮነቱን እንዲያጠናክር በማስተማርና በመምከር የድርሻችንን እንወጣለን ብለዋል። በዓሉን ስናከብር ለአካባቢያችን ብሎም ለሀገራችን ሠላምና አንድነት መጠበቅ የበኩላችንን ለመወጣት በመነሳሳት ሊሆን ይገባል ያሉት ዋና ፀሐፊው፤ ያለው ለሌለው በመረዳዳት፣ በመተጋገዝና በመተሳሰብ መሆን እንዳለበት አመልክተዋል። በዓሉን ለማክበር ከደቡብ ወሎ ዞን ተሁለደሪ ወረዳ የመጡት ሸህ አህመድ ዳውድ በበኩላቸው፤ የመወሊድ በዓልን ስናከብር ነብያችን ሰለ ሠላም አስፈላጊነት ለተከታዮቻቸው ያስተማሩትን በማሰብ ነው ብለዋል። ሠላም ከሌለ ወጥቶ መግባትና ሠርቶ መብላት ስለማይኖር ሠላምን ለማስከበር ሙስሊም አባቶች የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ አስታውቀዋል። ከወልዲያ ከተማ 06 ቀበሌ የበዓሉ ታዳሚ ወይዘሮ ፋጢሚ ሲራጅ በሰጡት አስተያየት፤ በዓሉን በደስታ እያሳለፉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዓሉ እያከብርን ያለው እርስ በእርስ በመረዳዳት ነው ብለዋል። የመውለድ በዓል በሰሜን ወሎ ዞን ሐብሩ ወረዳ ዳና መስጂድ በደማቅ ሥነ-ሥርዓት በተከበረበት ወቅት ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ የእምነቱ ተከታዮች ተሳትፈዋል።      
የመስቀል በዓል የአብሮነትና የተስፋ ተምሳሌት ነው”- የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤ አቶ አገኘሁ ተሻገር
Sep 27, 2023 38
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፦ “የመስቀል በዓል የአብሮነት እና የተስፋ ተምሳሌት ነው ሲሉ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈጉባኤ አቶ አገኘሁ ተሻገር ገለፁ። የእንኳን አደረሳችሁ ሙሉ መልዕክት እንደሚከተለው ቀርቧል፦ “የመስቀል በዓል በምድር ልምላሜ ደምቆና በአደይ አበባ ፈክቶ፣ በልጆች ባህላዊ ጨዋታ፣ በታላላቆች ምርቃትና ምስጋና ታጅቦ በአደባባይ ላይ በድምቀት የሚከበር በዓል ነው። በዓሉ በክረምቱ ደመና ተጋርዳ የቆየችው ፀሐይ ከምድር ልምላሜ ጋር ተዋሕዳ ደማቅ የብርሐን ጸዳል የምትጎናጸፍበት፣ ምድር የተሰጣትን ዘር አብቅላ እሸት መለገስ የምትጀምርበት፣ ሰዎች ከድባቴ ወጥተው አያሌ ተስፋዎች የሚሰነቁበት ወቅት በመሆኑ የተለየ ድምቀት አለው። ስለሆነም የመስቀል በዓል የአብሮነት፣ የትጋት፣ የጽናት፣ የትዕግሥትና የተስፋ ተምሳሌት ነው። እኛ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦችም በአብሮነት ጉዟችን የሚያጋጥሙንን ፈተናዎች በተስፋ፣ በትዕግሥት፣ በጽናትና በትጋት በማለፍ የኢትዮጵያን መፃዒ ዕድል ለማሳመር በቁርጠኝነት መነሣትና መሥራት ይጠበቅብናል። የመስቀል ደመራ ሲለኮስ ከፍተኛ ብርሃን፣ ታላቅ ድምቀት እና ውበት ይሰጣል፤ ተስፋንም ይሰንቃል። እኛ ኢትዮጵያዊያንም እንደ ደመራው ነን። እንደ ችቦው ተመሳሳይ ባህል፣ ቋንቋ፣ ስነልቦና እና ወጥ መልክአምድር ያላቸው ዜጎች ተሰባስበው ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች ሕዝቦች እንደ ችቦዎች ኅብር ፈጥረውና ተደምረው ታላቋን ኢትዮጵያን እውን እንድትሆን አድርገዋል። ችቦዎቹ ኅብር ፈጥረው እንዲቆሙ የሚያችሉት አምዶች ደግሞ አገር በጽኑ መሠረት ላይ እንድትቆም ከሚያደርጉ የጋራ እሴቶቻችን ጋር የሚመሳሰሉ ናቸው። በመሆኑም ተደምረንና ተጋምደን በአብሮነት ለሰላምና ለልማት መረጋገጥ ከተነሳን እንደ ደመራው ብርሃን ከፍ ብለንና ደምቀን እንታያለን። በዙሪያችን የከበበን የልዩነት ጨለማ ይገፈፋል። ስለሆነም በዓለም ቅርስነት ተመዝግቦ በተለያዩ የሀገሪቷ ክፍሎች በልዩ ልዩ ክንውኖች ታጅቦ የሚከበረው የመስቀል በዓል ከእርስ በርስ ግጭት፣ ከመጠላለፍ፣ ወንድም በወንድሙ ላይ ከመነሳሳት፣ ከመጨካከን እና ከሌሎችም አፍራሽ ተግባራት ራሳችን አርቀን በወንድማማችነት፣ በአብሮነት፣ በበጎነት፣ በመከባበር፣ በመደጋገፍና በመመካከር ለአገረ መንግሥት ግንባታና ለጋራ ዕድገት እንድንዘጋጅ በዚሁ አጋጣሚ መልዕክቴን አስተላልፋለሁ።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ ለመስቀል በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ
Sep 27, 2023 50
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ እንኳን ለ2016 ዓ.ም የደመራ እና የመስቀል በዓል በሰላም አደረሳችሁ ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል። ከንቲባዋ በመልዕክታቸው፣ “መስቀል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ሁሉ ያለምንም ልዩነት እስከ መሰቀል እና ሞት ድረስ ራሱን አሳልፎ የሰጠበት ተወዳዳሪ የማይገኝለት ፍቅር መገለጫ ነው” ብለዋል። “እኛም በመስቀሉ ላይ የተገለጠው የክርስቶስ የቤዛነት፣ የፍቅር እና እውነት መጠን፣ እርስ በእርስ በመዋደድ እና በመትጋት ከማይረቡ ጉዳዮች፣ እርስ በእርሳችን ከሚጋጩ እና ከሚያጠራጥሩን ሐሳቦች እና ድርጊቶች ርቀን በፍቅር፣ በአንድነት በመኖር እንደ ደመራ አሰባሳቢ ጥበብን እየገበየን፣ በዓመት አንዴ ደመራን ስናከብር ብቻ ሳይሆን በዕለት ተዕለት ሕይወታችን ውስጥ በተግባር እውነተኛ የመስቀሉ ወዳጆች መሆናችን በፍቅራችን እየገለጽን መኖር ይገባናል” ሲሉም አክለዋል። ሁላችንም ለከተማችን እና ለሀገራችን ሰላም እና ልማት ደመራችንን እንደምር ያሉት ከንቲባዋ፣ በዓሉ የፍቅር፣ የሰላም፣ የጤና እና የብልጽግና እንዲሆን ተመኝተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ብርሃነ መስቀሉን ምክንያት በማድረግ መልዕክት አስተላለፉ
Sep 27, 2023 108
አዲስ አበባ፤ መስከረም 16/2016 (ኢዜአ)፡- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ብርሃነ መስቀሉን ምክንያት በማድረግ መልዕክት አስተላልፈዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፦ እንኳን ለብርሃነ መስቀሉ አደረሳችሁ! ደመራ፣ መደመር፣ ደመረ፣ አከማቸ ማለት ነው፡፡ ደመራ የመለወጥ ምልክትነትም ነው፡፡ ለወንጀለኞች ስቅላት ይውል የነበረ መስቀል ዋጋና ምልክቱ የተለወጠበት ነው፡፡ ደመራ ብዙ ሰዎችን ሰብስቦ በኅብረት የሚያቆም ነው፡፡ ደመራ ባነሰው ላይ መጨመር ነው፡፡ ደመራ የተበተነውን መሰብሰብ ነው፡፡ የተዘረዘረ ነገርን የሚደምርና የሚያገናኝ ነው፡፡ ጸጋዬ ገ/መድኅን በግጥሙ… ነጋ አዲስ ዘመን ችቦ፤ ምድር ሕይወት አፈለቀች፤ የምሥራች አዝርዕቷን፤ አዲስ ቡቃያ ወለደች፤ የአደይ አበባን ለገሰች፣ ለአዲስ ዘመን አዲስ ብርሃን፤ አዲስ መስከረም ገበየች፣ …እንዳለው የአዲስ ዘመን ችቦ በአዲስ የፈካ ዘመን የሚጀመርበት ነው፡፡ የሰዎችም አዲስ ተስፋ አዲስ ጅምር የሚታይበት ነው፡፡ የመስቀል ወፍ የምትታሰርበት፤ አዝዕርት የሚበቅልበትም ነው፡፡ ደመራ ለበዓለ መስቀል ዋዜማ እንጨቶች የሚደመሩበት ነው፡፡ እንጨቶች ተሰብስበው ችቦ፤ ችቦዎች ተሰብስበው ደመራ የሚሆኑበት ነው፡፡ የችቦ እንጨቶችና ጭራሮዎች ምን ቢበዙ ወደ አንድ ካልመጡ ችቦ አይሆኑም። እንጨቶቹን የሚያስተሳሥራቸው የማሠሪያ ልጥ አለ፡፡ ችቦዎቹም በጋራ ተደጋግፈው ካልቆሙ ደመራ አይሆኑም። ችቦዎቹን አንድ አድርጎ የሚያቆማቸው የመሐሉ እንጨት አለ፡፡ ይህ እንጨት ጠንካራና በዙሪያው የተሰባሰቡትን ችቦዎች መሸከም የሚችል ነው፡፡ ይህ መሰሶ ኢትዮጵያን የሚወክልም ነው፡፡ የችቦው ሁሉም ጭራሮዎች አንድ ዓይነት አይደሉም፡፡ ከአንድ ቦታም አይለቀሙም፡፡ ሁሉም ችቦዎችም ተመሳሳይ አይደሉም፤ ከአንድ ቤት አይመጡም። ሁሉም እንጨቶች በየራሳቸው ይቆማሉ፤ ግን ደግሞ ብርታትና ጥንካሬ፣ ዐቅምና ጉልበት እንዲኖራቸው ችቦ ሆነው ይደመራሉ፡፡ እንጨቶቹን እንደሚያስተስሥረው ልጥ፣ ኢትዮጵያውያንን የሚያስተሣሥሩ ልዩ ልዩ ማንነቶች አሉ፡፡ ደመራ በመሰባሰብ የሀገራችንን ከፍታ እውን ለማድረግ የምንሰባሰብበት ተምሳሌታችን ነው፡፡ ኢትዮጵያ እንደ ችቦ እንጨቶች ብዙ ባህሎች፣ እምነቶች፣ ሀብቶች፣ ዕሴቶች፣ አመለካከቶች፣ ታሪኮች አሏት፡፡ ሁላችንም የግድ አንድ ዓይነት ማሰብ አይጠበቅብንም፤ የግድ ከአንድ ባህል፣ ከአንድ ቋንቋና ከአንድ ማንነት መገኘት አይኖርብንም። እነዚህን ሁሉ ጸጋዎች ከደመርናቸው፣ መጀመሪያ እንደ ችቦው አካባቢያዊ ዐቅም ይሆኑናል፡፡ ቀጥሎ ደግሞ እንደ ደመራው አስተሳሥረን በአንድ ዓምድ ላይ ካቆምናቸው ትልቅ ሀገር እንገነባለን፡፡ ይህ ችቦዎቹን አንድ አድርጎ የሚያቆመው የመሐል እንጨት አንድ የኢኮኖሚና የፖለቲካ ማኅበረሰብ የምንፈጥርበት የፌዴራል ሥርዓት ነው፡፡ ኅብረ ብሔራዊ አንድነታችን ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነታችን ነው፡፡ በዚህ የኢትዮጵያዊነትና የኅብረ ብሔራዊ አንድነት ደመራ፣ ግርማዋ የሚያስፈራ፣ የበለጸገች፣ ጠንካራ፣ ታላቅ የጋራ ሀገር መገንባት እንችላለን፡፡ የዚህ ሁሉ ቀመሩ ግን- እንደ ደመራው፣ መደመር ነው፡፡ ችቦውን በየግልና በየአካባቢያችን ልንሠራው እንችላለን፡፡ ደመራውን ግን በጋራ ካልሆነ አንደምረውም። የመጣንበት መንገድ ለየቅል ሊሆን ይችላል፡፡ እምነታችን፣ ምርጫችንና ምኞታችንም የየብቻችን ችቦ ሊሆን ይችላል። ሀገራችን ግን የጋራችን ደመራ ናት። ያለሁላችን አትኖርም። ምን ብንጓጓ ደመራውን ቸኩለን ለብቻችን አንለኩሰውም። የግድ ሌላውን እንጠብቃለን። እንደ ሀገር እንጂ እንደ ንዑስ አከባቢ፣ ወይም እንደ ሠፈር እኔና የኔ ብቻ ማለት አንችልም። ደመራው ለሁላችን በሚሆን ሥርዓት የሚመራ የሁላችንም ሀገር መስታወት ነው፡፡ ደመራው በኔ ችቦ በኩል ቀድሞ ይለኮስልኝ አንልም። ደመራው ሲለኮስም ‹የኔ ችቦ ትቀጣጠል› ይሆን ብለን አንሠጋም። ከየትም ይጀመር ከየት፣ ሙቀትና ብርሃኑ ለሁሉም እንጨቶችና ችቦዎች በሂደት ይዳረሳል፡፡ የኢትዮጵያ ሠናይ እሳት የሆነው የኢትዮጵያ ዕድገት፣ የትም መንደድ ቢጀምር፣ በጊዜ ሂደት ለሁላችን ይደርሳል፡፡ አንዱ እንጨት ለሌላው፣ አንዱ ችቦ ሌላው ብርሃን እንዲሆን በማጋራቱ ከእርሱ የሚጎድልበት ነገር የለም፡፡ ነገር ግን የሚጨምረው ዐቅም አለ፡፡ ሁሉም እየተለኮሱ በሄዱ ቁጥር፣ የብርሃኑ ዐቅም እየጨመረ ይሄዳል፡፡ እኛም ለሌላው ወገናችን ባካፈልን ቁጥር የሚጎድልብን ነገር የለም፡፡ የኢትዮጵያ ዐቅም ግን እየጨመረ፣ እየጠነከረ ይሄዳል፡፡ ትኩረታችን የገዛናት ወይም ሠርተን ያመጣናት ችቧችን ሳትሆን ትልቁ ደመራ ነው። የበዓሉ አመስጥሮ ያለውም ከዚሁ ነው፡፡ ችቦውን ልንገዛውና ልንሸጠው እንችላለን፡፡ ደመራው ግን ልክ እንደ ኢትዮጵያ ነው። አይሸጥም አይለወጥም። ሁሉም በግል ይዤው ልሂድ አይልም። እዚያው በጋራ ደምረን፣ በጋራ ልቦናችን ይዘነው የምንሄደው - የወል እውነታችን ነው። የኛነታችን ካስማችንም ጭምር ነው፡፡ ደመራ እውነተኛው መስቀል የተገኘበት ጠቋሚ ኮምፓስ ነው፡፡ ለሀገራችን እድገትና ብልጽግና በአንድነት የመቆም ምሳሌያችን ነው፡፡ ደመራ አቅጣጫ ነው፡፡ እውነተኛው መስቀል የተለየበት፡፡ ኢትዮጵያም ልጆቿ የሚቆሙበትና የሚሄዱበት እውነተኛ አቅጣጫ ለተስፋዋ ብርሃን፣ ለጥንካሬዋም ፈለግ ይሆናታል፡፡ ልክ መስቀሉን ፈልጎ ማግኘት እጅግ ከባድ ሆኖ ጊዜ እንደወሰደው ብልጽግናን መሻትም እንዲሁ ብዙ ድካምና ጥረት ይፈልጋል፡፡ መስቀሉን ማግኘት የብዙዎችን መተባበርና ምክር እንደመፈለጉ በሀገራችን ብልጽግናን ማረጋገጥም በዚሁ ልክ መተባበርና አብሮነትን መፈለጉ ከልቦናችን ይቀመጥ፡፡ የዘንድሮውን የደመራ በዓል እነዚህን ታላላቅ ዕሳቤዎች እያሰላሰልን እንደምናከብረው ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ መልካም የደመራና የመስቀል በዓል ለሁላችን ይሁን፡፡ ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!! ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ! መስከረም 16፣ 2016 ዓ.ም All reactions: 22
የመውሊድና የመስቀል ደመራ በዓላትን ስናከብር የመተሳሰብና የመረዳዳት ባህላችንን ይበልጥ በማጠናከር መሆን አለበት- ርእሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Sep 27, 2023 56
ሀዋሳ፤መስከረም 16 /2016 (ኢዜአ)፡- የመውሊድና የመስቀል ደመራ በዓላትን ስናከብር የመተሳሰብና የመረዳዳት ባህላችንን ይበልጥ በማጠናከር መሆን አለበት ሲሉ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ለመላው የክርስትና ዕምነት ተከታዮች እንኳን ለመስቀል ደመራ በዓል አደረሳችሁ ያሉ ሲሆን ለእስልምና እምነት ተከታዮችም እንኳን ለ1ሺ 498ኛው የመውሊድ በዓል አደረሳችሁ በማለት የመልካም ምኞት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በመልዕክታቸው ''የመውሊድና የመስቀል ደመራ በዓላትን ስናከብር ከአጠገባችን ያሉትን አቅመ ደካሞች በማሰብ መሆን ይገባል'' ብለዋል። በተለይም በሲዳማ ክልል የበዓሉ አክባሪዎች የተቸገሩትን በመርዳት፣ ያጡትን በመደገፍ፣ በመተሳሰብና ፍቅርን በመግለፅ እንዲያከብሩ ጥሪ አቅርበዋል። ሙስሊሙም ይሁን ክርስትያኑ በዓላቱን ሲያከብር የመተሳሰብና የመረዳዳት ባህልን ይበልጥ በሚያጠናክር መልኩ መሆን አለበትም ነው ያሉት። ''የበዓላቱን ዕሴቶች ከፍ በማድረግ አንድነታችንንና ህብረታችንን በሚያጎሉ ክንውኖች ማክበር ይገባልም ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም