ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
የቀዳማዊት እመቤት ጽሕፈት ቤት አራት የዓይነስውራን አዳሪ ትምህርት ቤቶችን ለመገንባት የድጋፍ ስምምነት ተፈራረመ
Feb 14, 2025 31
አዲስ አበባ፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፦ የቀዳማዊት እመቤት ጽሕፈት ቤት አራት የዓይነስውራን አዳሪ ትምህርት ቤቶችን መገንባት የሚያስችል የድጋፍ ስምምነት ተፈራረመ። ስምምነቱ የተከናወነው ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የካሊፍ ቢን ዛይድ አል-ናሃያን ፋውንዴሽን ጋር መሆኑ ተገልጿል። ስምምነቱን ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸውና እና የፋውንዴሽኑ ዳይሬክተር ጀነራል ሙሃመድ ሃጂ አልከሆሪ የተፈራረሙ ሲሆን በስምምነቱ ላይ ከተባበሩት አረብ ኤሜሬቶች የመጡ ሚኒስትሮችና ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የድጋፍ ስምምነቱ በተለያዩ የክልል ከተሞች ደረጃውን የጠበቀና ሙሉ መሰረተ ልማት የተሟላላቸው አራት የዓይነስውራን አዳሪ ትምህርት ቤቶችን ለመገንባት የሚያስችል መሆኑን የጽሕፈት ቤቱ መረጃ ያመለክታል። ቃሊቲ አካባቢ ተገንብቶ ከተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የመጡ ተማሪዎችን በማስተማር ላይ የሚገኘውን የዓይነ ስውራን አዳሪ ትምህርት ቤት ጽሕፈት ቤቱ በመሰል ድጋፍ ገንብቶ ማስረከቡ ይታወሳል።
በክልሉ በ4 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ውጪ ለቢሮ አገልግሎት መስጫ የሚውሉ ሕንጻዎችን ለመገንባት ስምምነት ተፈረመ
Feb 14, 2025 36
ቡታጅራ፤የካቲት 7/2017 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በሰባት የክላስተር ማዕከላት በ4 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ወጪ ለቢሮ አገልግሎት የሚውሉ ሕንጻዎችን ለማስገንባት ከሥራ ተቋራጮች ጋር የውል ስምምነት ተፈረመ። የግንባታ ውል ስምምነቱ የተፈረመው በክልሉ ከሚንቀሳቀሱ ሰባት ሥራ ተቋራጮች ጋር ነው። የክልሉ ቤተ መንግስትን ጨምሮ ሕንጻዎቹ በሆሳዕና፣ ቡታጅራ፣ ወራቤ፣ ወልቂጤ፣ሀላባ ቁሊቶ፣ዱራሜ እና ሳጃ ከተሞች እንደሚገነቡም ተገልጿል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ከተማ ልማትና ኢንዱስትሪ ክላስተር አስተባባሪና የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ስንታየሁ ወልደሚካኤል እንደገለጹት፥ የሕንጻዎቹ ግንባታ ሥራን ከ6 ወር እስከ 2 ዓመት ጊዜ ውስጥ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ለማብቃት ታቅዷል። በሰባት የክላስተር ማዕከላት የሚገነቡት ሕንጻዎች ሲጠናቀቁ በየማዕከላቱ የሚሰጠውን አገልግሎት እንደሚያቀላጥፉም ገልጸዋል። በተጨማሪም ለቢሮ ኪራይ የሚወጣን ወጪ በማስቀረት ለሌላ ልማት ለማዋል ያግዛል ብለዋል። የቢሮዎቹ ግንባታ ዲዛይን የክልሉን ህዝብ ባህላዊ እሴቶች ጠብቆ በዘመናዊ መልኩ የተዘጋጀ መሆኑንም አመልክተዋል። የሕንጻዎች ግንባታ የክልሉን ክላስተር ከተሞች እድገት በማፋጠን፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠርና ኢንቨስትመንትን በማበረታታት መነቃቃትን እንደሚፈጥርም ተናግረዋል። የሕንጻዎቹ ግንባታ ሥራ በሚፈለገው ጥራትና በታቀደለት የጊዜ ገደብ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ በክልሉ በኩል ተገቢ ክትትል እንደሚደረግም አቶ ስንታየሁ ገልጸዋል። በስምምነቱ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ልዩ አማካሪ አቶ ንጉሴ አስረስ፣የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሰማን ሽፋን እና የሥራ ተቋራጮች ተገኝተዋል።
በክልሉ የመማር ማስተማር ሂደት ላይ እያጋጠመ ያለውን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ሁሉም የበኩሉን ሚና ሊወጣ ይገባል
Feb 14, 2025 33
ባህርዳር፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የመማር ማስተማር ሂደት ላይ እያጋጠመ ያለውን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ሁሉም የበኩሉን ሚና ሊወጣ እንደሚገባ በክልሉ ምክር ቤት የሴቶች፣ ህፃናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴ የተማሪዎችን ተሳትፎ ማጠናከር የሚያስችል የንቅናቄ የውሳኔ ሃሳብ ላይ ተወያይቶ አቅጣጫ አስቀምጧል። በምክር ቤቱ የሴቶች፣ ህፃናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ አበራሽ ታደሰ፤ የውሳኔ ሃሳቡ ያስፈለገበትን ዝርዝር ሁኔታ ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። በማብራሪያቸውም በክልሉ አንዳንድ አካባቢዎች የመማር ማስተማር ሂደት ላይ እያጋጠመ ባለው ችግር መስተጓጎል እየገጠመው መሆኑን አንስተዋል። ከቅድመ መደበኛ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ድረስ መንግስት የትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው በዚህ ረገድ የምክር ቤት አባላት የላቀ ሚናቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል። የምክር ቤት አባላት በተለይም በተመረጡባቸው አካባቢዎች በትምህርት ዘርፉ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮች በዘላቂነት እንዲፈቱ የህብረተሰቡ እገዛና ትብብር እንዲጠናከር ሊሰሩ ይገባል ብለዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ በክልሉ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እየተፈጠረ መሆኑን ጠቅሰው የመማር ማስተማር ሂደቱን ይበልጥ ማጠናከር የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን ገልፀዋል። በክልሉ የመማር ማስተማሩ ሂደት የተሳለጠ እንዲሆንና የተማሪዎችን የማቋረጥ ምጣኔ ለመቀነስ ከወላጆች ጀምሮ የሁሉም እገዛና ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል ብለዋል። በዚህ ረገድ የምክር ቤት አባላትም የላቀ ሚናቸውን እንዲወጡ ርዕሰ መስተዳድሩ ጠይቀዋል። ለአራት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የክልሉ ምክር ቤት 9ኛ መደበኛ ጉባኤ የተለያዩ አዋጆችን እና የዳኞችን ሹመት በማፅደቅ ዛሬ ተጠናቋል።
የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን ለማረጋገጥ የሚቀረጹ ፕሮግራሞችን በተጠናከረ አግባብ መተግበር ይገባል
Feb 14, 2025 27
መቱ፤የካቲት 7/2017 (ኢዜአ) የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን ለማረጋገጥ የሚቀረጹ ፕሮግራሞችን በተጠናከረ አግባብ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ ጤና ሚኒስቴር አስታወቀ። አገር አቀፍ የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ጥራት ጉባኤና የጤና ስርዓት ማነቅዎች መማማሪያ ፕሮግራም መድረክ በመቱ ካርል ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል እየተካሄደ ነው ። በመድረኩ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር አየለ ተሾመ፣ የኦሮሚያ ክልል ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዶክተር ቦኮና ጉታን ጨምሮ የሁሉም ክልሎች ጤና ቢሮዎች አመራሮችና ከተለያዩ ሆስፒታሎች የመጡ የሕክምና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው ። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር አየለ ተሾመ በወቅቱ እንደተናገሩት የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን ለማረጋገጥ የሚቀረጹ ፕሮግራሞች በየተቋማቱ ባሕል ሆነውና ተጠናክረው መተግበር ይኖርባቸዋል። ሚኒስቴሩ፥ በዘርፉ የክትትልና የድጋፍ ስራን በመደበኛነት እንደሚያከናውን አመልክተዋል። በሂደቱም ድክመቶችን በመለየት እንዲፈቱና ጠንካራ ጎኖችም እንዲስፋፉ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አስታውቀዋል ። የኦሮሚያ ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዶክተር ቦኮና ጉታ በበኩላቸው በክልሉ በአገልግሎት አሰጣጥ፣ በጤና መድህን ሽፋንና በክትትልና ድጋፍ ዘርፎች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይ ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የጤና ተቋማትን በሰው ኃይልና በግብአት አቅርቦት ከማሟላት ጎን ለጎን ተገልጋይ እና አገልጋይን ለሚያገናኘው የሪፎርም ስራ ትኩረት መሰጠቱን አመልክተዋል። የመቱ ካርል ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ ዶክተር ሶላን በቀለ “በሆስፒታሉ የተሟላ የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ጥራትን ለማረጋገጥ የተቀረጹ ኢኒሼቲቮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው” ብለዋል። ሆስፒታሉ ከኢሉ አባቦር ዞን በተጨማሪ ከቡኖ በደሌ ዞን እንዲሁም ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦችና ከጋምቤላ ክልሎች ለሚመጡ ታካሚዎች አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን አስታውቀዋል። የመድረኩ ተሳታፊዎች የመቱ ካርል ኮምፕርሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታልን የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ተመልክተዋል።
የክልሉ ስፖርት በራሱ አቅም ገቢ በማመንጨት እየተጠናከረ እንዲሄድ በትኩረት ይሰራል - ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን(ዶ/ር)
Feb 14, 2025 21
ባህር ዳር፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፡- የክልሉ ስፖርት በራሱ አቅም ገቢ በማመንጨት እየተጠናከረ እንዲሄድ በትኩረት እንደሚሰራ የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የክልሉ ስፖርት ምክር ቤት ሰብሳቢ አብዱ ሁሴን(ዶ/ር) አስታወቁ። የክልሉ ስፖርት ምክር ቤት 26ኛ ጠቅላላ ጉባኤውን በባህር ዳር ከተማ አካሂዷል። ማምሻውን በጀመረው የምክር ቤቱ ጠቅላላ ጉባኤ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋዬን ጨምሮ የክልልና የዞን አመራሮች፣ የምክር ቤቱ አባላትና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። የክልሉ ምክትል ትዕሰ መስተዳድርና የምክር ቤቱ ሰብሳቢ አብዱ ሁሴን(ዶ/ር) በጉባኤው ላይ እንደገለጹት ስፖርት አሁን ላይ የአካባቢን ገጽታ በመገንባትና የኢንቨስትመንት ምንጭ እየሆነ መጥቷል። በተለይም በክልሉ ጤናማና አምራች ዜጋ ለማፍራት ድርሻው የጎላ መሆኑን ጠቅሰው ለዚህም የክልሉ አመራርና የስፖርት ምክር ቤቱ አባላት ዘርፉ ህዝባዊ መሰረት ይዞ እንዲያድግ መስራት ይገባል ብለዋል። የስፖርት ዘርፉ ከመንግስት ጥገኝነት ወጥቶ በራሱ አቅም ገቢ በማመንጨት እየተጠናከረ እንዲሄድ በጋራ አቅዶ መስራትና የተጠናከረ እገዛ ማድረግ ያስፈልጋል ሲሉ ተናግረዋል። የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን ማስፋፋትና ስፖርቶችን በማበረታታት ጤናማ ትውልድ መፍጠርም ያስፈልጋል ነው ያሉት። የክልሉ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ሃላፊና የምክር ቤቱ ምክትል ሰብሳቢ አቶ እርዚቅ ኢሳ በበኩላቸው አዳዲስና ተተኪ ስፖርተኞችን በማፍራት፣ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን የማስፋፋት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። በጉባኤው የስፖርት ምክር ቤቱ የ25ኛው የምክር ቤቱ ቃለ ጉባኤ ቀርቦ የጸደቀ ሲሆን በሌሎች ተተኳሪ ነጥቦች ላይ ውይይት እየተደረገ ነው።
ህገወጥ የነዳጅ ግብይትን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ህብረተሰቡ ተሳትፎውን እንዲያጠናክር ተጠየቀ
Feb 14, 2025 18
ደብር ብርሃን፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፦በደብረ ብርሃን ከተማ ህገወጥ የነዳጅ ግብይትን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ህብረተሰቡ ተሳትፎውን በማጠናከር ለቁጥጥርና ክትትል ተግባሩ ስኬታማነት የበኩሉን እንዲወጣ የከተማ አስተዳደሩ ጠየቀ። የከተማ አስተዳደሩ በህገወጥ የነዳጅ ዝውውርና ስርጭትን ለመከላከል በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሂዷል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ወርቃሐማሁ ኮስትሬ በውይይቱ ላይ ነዳጅን በአግባቡ ማሰራጨትና መጠቀም እንደሚገባ ተናግረዋል። በመንግስት ከፍተኛ የውጪ ምንዛሬ የሚገባውን ነዳጅ በህገ ወጥ መንገድ ከማዳያዎች በማውጣት የሚያከማቹና የሚቸረችሩ ግለሰቦች እጥረት ከመፍጠር ባለፈ በዚህ ምክንያት በንብረትና በሰው ህይወት ላይ ጉዳት እየደረ ነው ብለዋል። አሁን ላይ ህገ ወጥ የነዳጅ ግብይትና ሰርጭትን መከላከል የከተማ አስተዳደሩ ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው ህብረተሰቡ ህገወጦችን እንዲያጋልጥ ጠይቀዋል። የከተማ አስተዳደሩ ንግድ መምሪያ ሃላፊ ወይዘሮ ይርጋለም ምስጋናው በበኩላቸው የህገወጥ ንግድን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ከሚሰራባቸው ዘርፎች የነዳጅ ጉዳይ አስቸጋሪ እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል። አንዳንድ ነዳጅ ማደያዎች ህገወጥነትን ከመታገል ይልቅ ችግሩ እንዲባባስ እያደረጉ እንዳለ ጠቅሰው ባለፉት 7 ወራት 7 ሺህ 293 ሊትር ናፍጣና ቤንዚል በህገወጥነት ሲቀሳቀስ መያዙን ተናግረዋል። በከተማው የሚገኘው 'የኒወን' ነዳጅ ማደያ ስራ አሰኪያጅ እድማሱ በላይ፣ ህግ ወጥ ድርጊት የሞሳተፉትን ለይቶ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ አመልክተዋል። የኖክ ማደያ ስራ አስኪያጅ አቶ የሺዋስ ታደሰም እንዲሁ ችግሩን ለመፍታት በጋራ መስራት አስፋለጊ መሆኑ በህገ ወጥ መልኩ የሚንቀሳቀሱትን ማጋለጥ እንደሚገባ ተናግረዋል።
በአፍሪካ ለዜጎች ጥራት ያለው ትምህርት ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት ሊሰራ ይገባል - ኮሚሽነር መሐመድ ቤልሆሲን(ፕሮፌሰር)
Feb 14, 2025 24
አዲስ አበባ፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፡- በአፍሪካ ሀገራት የትምህርት ተደራሽነትን ለማስፋት እና ጥራት ያለው ትምህርትን ለዜጎች ተደራሽ ማድረግ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባ በሕብረቱ የትምህርት፣ የሳይንስ፣ የቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኮሚሽን ገለጸ። 38ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ነገ እና ከነገ በስትያ በአዲስ አበባ ይካሄዳል። የኮሚሽኑ ኮሚሽነር መሐመድ ቤልሆሲን(ፕሮፌሰር) ኮሚሽኑ የተለያዩ ስትራቴጂዎችን በትምህርት፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ እንዲሁም በቴክኒክና ሙያ ቀርጾ እየተገበረ መሆኑን ተናግረዋል። የመማር ማስተማርን ለማጠናከር እና ጥራት ያለው ትምህርት በአህጉሪቱ ተደራሽ ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። ሁሉንም ህብረተሰብ ተደራሽ የሚያደርግ ትምህርት ለዜጎች መስጠት የሚያስችል የትምህርት ፖሊሲና ስትራቴጂ ተቀርጾ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህም ውጤት እየተገኘ ነው ብለዋል። ጥራት ያለውና ሁሉንም የሚያካትት ትምህርት ለዜጎች መሥጠት ላይ እየተሰሩ ያሉ ስራዎች እንዲጠናከሩ አሁንም ትኩረት እንደሚፈልግ ጠቅሰዋል። ከአፍሪካ ውጪ ካሉ ሀገራት ጋር ግንኙነት እና ስምምነት በመፍጠር የትምህርት ተደራሽነትን ለማጠናከር እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። ዘርፉን መደገፍ የሚያስችሉ፣ በቴክኒክ እና ሙያ ጥራት ያለው ትምህርትን በመስጠት በዲጂታል መንገድ የተጀመሩ ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸውም ጠቁመዋል። የተቀረጸውን የአፍሪካን ትምህርት አጀንዳ ሁሉም ሀገራት በመተግበር ጥራት ያለው ትምህርት ለአህጉሪቱ ዜጎች ማዳረስ ላይ በትኩረት ሊሰሩ ይገባል ብለዋል። የዲጂታል መሠረተ ልማትን ተደራሽ ለማድረግ ጊዜ የሚወስድ ቢሆንም ሀገራት ለትምህርት የሚያስፈልገውን ሀብት በመመደብ ጥራት ላይ ያለውን ችግር ለመፍታት መስራት እንደሚገባም ገልጸዋል። በኢኖቬሽን ላይ የተጀመሩ ሥራዎችን የበለጠ ለማጠናከር እና ለዲጂታል ትምህርት ትኩረት መስጠት እንደሚያስፈልግም አንስተዋል።
በክልሉ ባለፉት ሦስት ዓመታት የተገኘው ኢኮኖሚያዊ ውጤት ወጪን በራስ የመሸፈን አቅም አሳድጓል
Feb 14, 2025 35
ሚዛን አማን፤የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፡-በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ባለፉት ሦስት ዓመታት የተመዘገበው ኢኮኖሚያዊ ውጤት ወጪን በራስ የመሸፈን አቅም ማሳደጉ ተገልጿል። የብልጽግና ፓርቲ ሁለተኛ ጉባኤ ላይ የተቀመጡ የሥራ አቅጣጫዎችና ውሳኔዎች ላይ ያተኮረ የቤንች ሸኮ ዞን አመራሮች የተሳተፉበት ውይይት በሚዛን አማን ከተማ ተካሂዷል። የብልጽግና ፓርቲ ስራ አሰፍጻሚ አባል፣የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው በዚህ ወቅት እንዳሉት ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሥራ አዎንታዊ ውጤት እያስመዘገበ ነው። ለአብነት ከሦስት ዓመታት በፊት በዓመት ከክልሉ ይሰበሰብ የነበረው የገቢ መጠን ከ2 ቢሊዮን ብር ያልዘለለ ሲሆን አሁን ላይ በተፈጠረው ጠንካራ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሥራ 10 ቢሊዮን ብር ማድረስ መቻሉን ጠቅሰዋል። በዚህም የክልሉን ወጪ በራስ የመሸፈን አቅምን 60 በመቶ ማድረሱን ጠቅሰው፥ እያደገ የመጣውን የምርት አቅም የሚመጥን ገቢን የመሰብሰቡ ተግባር ይጠናከራል ብለዋል። በቀጣይ በአካባቢው ያለው የተፈጥሮ ሀብት ከክልሉ አልፎ የሀገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ የራሱን አስተዋጽኦ እንዲያበርክት በትኩረት ይሰራል ብለዋል። በተለይ የቅመማ ቅመም ምርቶችን በተደራጀ መልኩ አምርቶ ለገበያ በማቅረብ ከቡና በተጨማሪ የወጪ ምርቶችን ለማሳደግ እንደሚሠራ ጠቁመዋል። በአካባቢው የሚመረቱ የግብርና ምርቶች የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር ለግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪዎች ግብዓት እንዲሆኑ በስፋት ይሰራል ብለዋል። የቤንች ሸኮ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን በበኩላቸው፥ በኢኮኖሚ ዘርፍ የተቀመጡ ግቦች እንዲሳኩ ብልሹ አሰራሮችን መታገል የሁሉም ድርሻ መሆን አለበት ብለዋል። የአካባቢን ሀብትና ምቹ ሁኔታን ለይቶ በመረዳት በምግብ ራስን ለመቻል በልዩ ትኩረት እየተሠራ መሆኑንም ጠቁመዋል። ከውይይቱ ተሳታፊ አመራሮች መካከል አቶ ኮጁ በዳካች፤ የኑሮ ውድነትን ማረጋጋት የሚያስችሉ የምርት አቅርቦትና የሰንበት ገበያዎችን ማጠናከር እንደሚገባ አንስተዋል። ሌላው የውይይቱ ተሳታፊ ወይዘሮ ብርሃኔ በዛብህ፤ ''ለአካባቢው ለውጥ መሥራት ይጠብቅብናል'' ብለዋል። ለአስተማማኝ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት የመልካም አስተዳደር ጥያቄ የሚያስነሱ የመሠረተ ልማት ዝርጋታ ሥራዎች ላይ ትኩረት መደረግ እንዳለበትም ተናግረዋል።
የአሶሳ አጠቃላይ ሆስፒታል ኦክስጂን ማምረት መጀመሩ የአገልግሎት አሰጣጡን አሻሽሎታል
Feb 14, 2025 93
አሶሳ፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፦ የአሶሳ አጠቃላይ ሆስፒታል ኦክስጂን ማምረት መጀመሩ የጤና አገልግሎት አሰጣጡ እንዲሻሻል ማድረጉን ሆስፒታሉ አስታውቋል። የሆስፒታሉ ሜዲካል ዳይሬክተር ዶክተር መርቀኒ አወድ እንደገለፁት፤ የኦክሲጅን ምርቱ የሆስፒታሉን የጤና አገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል አግዟል። ከዚህ ቀደም ሆስፒታሉ የኦክሲጅን አቅርቦትን ከአዲስ አበባ እና ነጆ በማስመጣት ሲጠቀም በመቆየቱ ከፍተኛ ወጪ ያወጣ ነበር ያሉት ዳይሬክተሩ በዚህም ምክንያት የተሻለ ህክምና ለማግኘት ወደ ሌላ ክልል የሚሄዱ ታካሚዎች በሚገጥማቸው እንግልት ፈታኝ ጊዜን አሳልፈዋል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በሆስፒታሉ የሚመረተው ኦክሲጅን ተገልጋዮች ተገቢውን ህክምና እንዲያገኙ በማድረግ የሆስፒታሉን አገልግሎት አሰጣጥ እንዲሻሻል ማድረጉንም ጠቁመዋል። ሆስፒታሉ ለቀዶ ጥገና፣ ለእናቶች እና ህፃናት ህክምና እንዲሁም ኦክስጂን ለሚያስፈልጋቸው ህሙማን በበቂ ሁኔታ ኦክሲጅንን እያመረተ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህም በተጨማሪ በክልሉ እና በአጎራባች አካባቢዎች ለሚገኙ ሆስፒታሎች እና ጤና ተቋማት በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረበ መሆኑን ገልፀው ይህም ለሆስፒታሉ የገቢ አቅምን እየፈጠረ መሆኑን አመልክተዋል። ከኦክስጂን በሚሰበሰበው ገቢ ተጨማሪ ማስፋፊያ ለመስራት የኦክሲጅን አጠቃቀም መመሪያ መዘጋጀቱንም ዶክተር መርቀኒ አብራርተዋል። በሆስፒታሉ የባዮ ሚዲካል ባለሙያ ተስፋዬ ደሳለኝ በበኩላቸው ሆስፒታሉ በቀን ከ80 በላይ ሲሊንደር በማምረት በስሩ የሚገኙ የጤና ተቋማትን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ገልፀዋል። የአሶሳ አጠቃላይ ሆስፒታል በአሶሳ እና አካባቢው እንዲሁም ከአጎራባች ኦሮሚያና እና ከሱዳን ሀገር ለሚመጡ ታካሚዎች አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።
የአማራ ክልል ምክር ቤት የዳኞችን ሹመት አፀደቀ
Feb 14, 2025 38
ባህርዳር ፤ የካቲት 7/2017 (ኢዜአ)፦የአማራ ክልል ምክር ቤት የ229 ዳኞችን ሹመት አጸደቀ ። ምክር ቤቱ በክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ዓለምአንተ አግደው የቀረቡለትን የዳኞች ሹመት አጽድቋል ። ሹመታቸው ከጸደቀላቸው መካከልም ሶስቱ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ሆነው የተሾሙ ናቸው። ዘጠኝ ዳኞች ደግሞ ለክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ለደብረ ማርቆስ ምድብ ችሎት እንዲሁም 46 የከፍተኛ ፍርድ ቤትና 171 የወረዳ ፍርድ ቤት ዳኞች ሆነው የተሾሙ ናቸው ። በዛሬው እለት ሹመታቸው ከፀደቀላቸው ዳኞች መካከል 43ቱ ሴቶች መሆናቸውም ተመላክቷል። ተሿሚዎቹ የተሻለ የትምህርት ዝግጅት ያላቸውና ህዝብን በቅንነትና በታማኝነት ያገለግላሉ ተብሎ ዕምነት የተጣለባቸው እንደሆኑም ተመላክቷል። ምክር ቤቱ የስነ-ምግባር ግድፈት ፈፅመዋል የተባሉ ሁለት ዳኞችን ከስራ እንዲሰናበቱ በአብላጫ ድምፅ ወስኗል። ምክር ቤቱ ለአራት ቀናት ያካሄደውን 9ኛ መደበኛ ጉባኤ የአማራ ክልል ፍርድ ቤቶች ማጠናከሪያ ረቂቅ አዋጅን፣ የክልሉን የባህል ፍርድ ቤቶችን ለማቋቋምና ዕውቅና ለመስጠት የወጣውን ረቂቅ አዋጅ ጨምሮ ሌሎች ልዩ ልዩ አዋጆችን መርምሮ በማጽደቅ ዛሬ አጠናቋል ።
የሀረሪ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከያ ማዕከል የግብዓት ድጋፍ ተደረገለት
Feb 14, 2025 39
አዲስ አበባ፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፦ የሀረሪ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከያ ማዕከል ከክልሉ አካባቢ ጥበቃ ባለ ስልጣን 3ነጥብ 5 ሚሊዩን ብር ግምት ያላቸው የድንገተኛ እሳት አደጋ ቁጥጥር ትጥቅና መሳሪያ ድጋፍ ተደረገለት። ድጋፉን የክልሉ አካባቢ ጥበቃ ባለ ስልጣን ሃላፊ አቶ ሰሚር በክሪ በዛሬው እለት ለክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ረምዚ ሱልጣን አስረክበዋል። ኮሚሽነር ረምዚ ሱልጣን ድጋፉን በተረከቡበት ወቅት እንደገለፁት ድጋፉ ማዕከሉን በትጥቅ በማደራጀት ፈጣን እና ውጤታማ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል ነው። በየትኛውም ቦታ እና አጋጣሚ ሊከሰቱ ለሚችሉ የእሳት አደጋዎች ፈጣን ምላሽ በመስጠት የዜጎችን ህይወትና ሃብት ለመታደግ ከፍተኛ አበርክቶ እንደሚኖረውም ጠቁመዋል። ማዕከሉ የድንገተኛ እሳት አደጋ ቁጥጥር ትጥቅና የመከላከያ ቁሶችን ማግኘቱ ከህዝብ ለሚቀርቡ የአገልግሎት ጥያቄዎች ፈጣንና ቀልጣፋ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል መሆኑንም ገልፀዋል። የሀረሪ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለ ስልጣን ሀላፊ አቶ ሰሚር በክሪ በበኩላቸው እንደገለጹት ባለስልጣኑ 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ግምት ያላቸውን የእሳት አደጋ ትጥቅና መሳሪያ ድጋፍ ማድረጉ ስራውን የበለጠ ለማገዝ በማሰብ ነው። ባለ ስልጣን መስሪያ ቤቱ ማዕከሉ የሚሰጠውን አገልግሎት ለማጎልበት መሰል ድጋፎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም መግለጻቸውን ከክልሉ ኮሙኒኬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በፍትህ ዘርፉ የዜጎችን የአገልግሎት እርካታ ለማሳደግ የተከናወነው የአሰራር ማሻሻያ ለውጥ እያመጣ ነው
Feb 14, 2025 39
ጅግጅጋ፤ የካቲት 7/2017 (ኢዜአ)፦ በፍትህ ዘርፉ የዜጎችን የአገልግሎት ፍላጎት ለማርካት የተከናወነው የአሰራር ማሻሻያ ለውጥ እያመጣ መሆኑን የፍትህ ሚኒስትር ሐና አርዓያስላሴ ገለጹ። ጠንካራ የፍትሕ አካላት ቅንጅት ለተረጋገጠ የህዝብ አመኔታ በሚል መሪ ሃሳብ ሰባተኛው የፍትሕ ሚኒስቴርና የክልል የፍትሕ ቢሮዎች የጋራ ጉባዔ በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ከተማ በመካሄድ ላይ ነው። በጉባዔው የተገኙት የፍትሕ ሚኒስትር ሐና አርዓያስላሴ እንዳሉት ባለፉት የለውጥ ዓመታት የፍትሕ ስርዓቱን ለማሻሻል የተከናወነው የሪፎርምና የህግ ማሻሻያ ስራም ሰብዓዊ መብትን ያረጋገጠ የፍትህ ስራ እንዲከናወንና በህዝብ ዘንድ የሚነሱ ቅሬታዎችን እየቀረፈ ነው። በተለይ የባህላዊ የፍትህ ስርዓቶች እውቅና መስጠትና በአስተዳደር ፍትህ ላይ የተደረገው የለውጥ ስራም ውጤት ማስመዝገቡን ጠቅሰዋል። የተረጋገጠና ህዝባዊ አመኔታ ያለው የፍትህ ስርዓት ለመገንባት የሚከናወኑ ተግባራትን ለማጎልበት ብዙ የሚቀሩ ስራዎች እንዳሉ የጠቆሙት ሚኒስትሯ በአዲስ እይታና በቁርጠኝነት የፍትህ ዘርፉን የማጎልበት ስራ ማከናወን ይገባልም ብለዋል። በተለይ በሶስት ዓመቱ የትራንስፎርሜሽን ዘመን እና በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የተከናወኑ ጠንካራ ስራዎችን ማስቀጠልና ውስንነቶችን መቅረፍ የጉባዔው ዋንኛ ተግባር መሆኑን አመልክተዋል። የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ መሀመድ በበኩላቸው ከለውጡ ዓመታት በፊት በክልሉ ዜጎች አላግባብ የሚታሰሩበት፣ የሚሰቃዩበት የሚንገላቱበት ለሞት፣ ለአካልና ስነ-ልቦና ጉዳት የሚዳረጉበት እንደነበር ጠቅሰዋል። ከለውጡ ማግስት በተከናወነው የፍትህ ስራ የሰብዓዊ መብት ጥበቃ ስራዎች የጎለበተበት፣ የዜጎች እንግልትና ስቃይ የተቀረፈበት መሆኑን ጨምሮ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ህገ መንግስታዊ መብቶች እየተከበሩ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ የሚከናወኑ የልማት፣ የመልካም አስተዳደርና የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታና የህዝብ ተጠቃሚነት እየጎለበተ መምጣቱን የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ ለዚህም የፍትህ አካላቱ ያበረከቱት ሚና ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰዋል። በጉባዔው ላይ ሚኒስትር ዴኤታዎችና የሚኒስትር መስሪያ ቤቱ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ የክልል የፍትህ እና አቃቢ ህግ ቢሮ ሃላፊዎች፣ የፖሊስ ኮሚሽነሮችና ሌሎች የስራ ሃፊዎች ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያና ቻይና በፍትሕ ዘርፍ በትብብር ለመስራት ተስማሙ
Feb 14, 2025 52
አዲስ አበባ፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና ቻይና በፍትህ ዘርፍ በትብብር መስራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። የመግባቢያ ስምምነቱን በኢትዮጵያ በኩል የፍትህ ሚኒስትሯ ወይዘሮ ሐና አርአያስላሴ የፈረሙ ሲሆን በቻይና በኩል ደግሞ የህዝባዊት ቻይና ሪፐብሊክ የፍትህ ሚኒስትር ሂ ሮንግ ፈርመዋል። ስምምነቱ ሁለቱ ሀገራት በፍትህ ዘርፍ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎችን ለማመቻቸት፣ በፎርንሲክ ምርመራ፣ በግልግል ዳኝነት፣ በነጻ የህግ ድጋፍ ዙሪያ የልምድ ልውውጥ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑም ተገልጿል። እንዲሁም የፍትህ ዘርፉን ለማዘመን የሚያስችሉ የቴክኖሎጂ ልውውጦችን ለማድረግ፣ ለባለሙያዎች የትምህርት ዕድል ለመፍጠርና በሁለቱ ሀገራት ፍትህ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች መካከል የተቋማት ጥምረት በመፍጠር በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸው ነውም ተብሏል፡፡ አሁን የተፈረመው የመግባቢያ ሰነድም በሁለቱ ሀገራት ተቋማት መካከል ቀደም ሲል በፍትህ ዘርፍ የነበረውን ትብብር የሚያጠናክር መሆኑን ኢዜአ ከፍትህ ሚኒስቴር ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
ሰባተኛው የፍትሕ ሚኒስቴርና የክልል የፍትሕ ቢሮዎች የጋራ ጉባዔ በጅግጅጋ ከተማ በመካሄድ ላይ ነው
Feb 14, 2025 37
ጅግጅጋ ፤የካቲት 7/2017 (ኢዜአ)፡- ሰባተኛው የፍትሕ ሚኒስቴርና የክልል የፍትሕ ቢሮዎች የጋራ ጉባዔ በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ከተማ እየተካሄደ ነው። የጋራ ጉባዔው “ጠንካራ የፍትሕ አካላት ቅንጅት ለተረጋገጠ የህዝብ አመኔታ” በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ ነው ። በጉባዔው ላይ የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ መሀመድ፣ የፍትሕ ሚኒስትር ሐና አርዓያስላሴ፣ ሚኒስትር ዴዔታዎችና የሚኒስትር መስሪያ ቤቱ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል። እንዲሁም የክልል የፍትህና አቃቢ ህግ ቢሮ ሃላፊዎች፣ የፖሊስ ኮሚሽነሮችና ሌሎች የስራ ሃላፊዎች ተሳትፈዋል። ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ጉባዔ የፍትሕ ሚኒስቴርና የክልል ፍትህ ቢሮዎች የ2017 በጀት ዓመት የግማሽ ዓመት የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ቀርቦ ውይይት ይደረግበታል።
የኮሪደር ልማቱን ጨምሮ የመዲናዋ ልማት ስራዎች አካል ጉዳተኞችን ያማከሉ ናቸው- አካል ጉዳተኞች
Feb 14, 2025 36
አዲስ አበባ፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ):- ባለፉት ዓመታት የኮሪደር ልማቱን ጨምሮ በሁሉም ዘርፎች አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ያደረጉ የልማት ሥራዎች በስፋት መከናወናቸው ኢዜአ ያነጋገራቸው አካል ጉዳተኞች ገለፁ። አዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ አካል ጉዳተኞች መካከል አቶ ከተማ ባይለየኝ፣ ወይዘሮ አለሚቱ ተፈራና አቶ አድባሩ ይገርማል ከዚህ በፊት በመዲናዋ መንገዶች በየጊዜው የሚደረጉ መቆፋፈሮች አስቸጋሪና ላልታሰበ አደጋ የሚዳርጉ ነበሩ። በተለይም ዐይነ ስውራን ክፍት በተተው ጉድጓዶች እየወደቁ ሕይወት እስከማጣት የሚደርስ ተጨማሪ ጉዳት መዳረጋቸውን አንስተዋል። በእግረኛ መንገዶች ላይ የሚከማቹ የግንባታ ተረፈ ምርቶችና የወደቁ ቁሳቁሶች የአካል ጉዳተኛን እንቅስቃሴ የሚገድቡ እንደነበሩ ገልጸዋል። ዐይነ ስውራን በእግረኛ መንገድ ላይ ከሚተከሉ ዛፎች እና የመብራት ምሰሶዎች ጋር የመጋጨት ዕድላቸው ሰፊ እንደነበርም እንዲሁ። የኮሪደር ልማቱ ግን ይስተዋሉ የነበሩ ክፍተቶችን በማረም አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ አድርጎ መገንባቱን ጠቅሰው፤ አመስግነዋል። በእግረኛ መንገዶች የነበሩ የግንባታ ተረፈ ምርቶች መወገዳቸው እና ለዐይነ ስውራንና ለአካል ጉዳተኛ መንቀሳቀሻ ቢጫ ምልክቶች መገፋፋትን በማስቀረት በነጻነት እንዲጓዙ ማስቻሉን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ዐይነ ስውራን ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ አበራ ረታ ቀደም ባሉ ጊዜያት ጉድጓዶች፣ የመብራትና የስልክ ምሰሶዎች ተጨማሪ የአካል ጉዳት ያስከትሉባቸው እንደነበረ ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ ባለፉት አምስት ዓመታት ኮሪደር ልማትን ጨምሮ በሁሉም ዘርፎች የተከናወኑ የልማት ስራዎች አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ እንደሆኑ ገልጸዋል። የልማት ፕሮጀክቶች ምቹ አካባቢን በመፍጠር፣ በትምህርት ተደራሽነትና በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ያደረጉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ጥረቶች ውጤት እንዲያመጡ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ መጠናከር አለበት
Feb 14, 2025 44
ደምቢ ዶሎ፤ የካቲት 7/2017 (ኢዜአ)፡-የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ጥረቶች ውጤት እንዲያመጡ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ መጠናከር እንዳለበት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሃብት ሥራ ስምሪትና የቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) ገለጹ። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሃብት ሥራ ስምሪትና የቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) እና ሌሎች የኮሚቴው አባላትና የኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ የሥራ ሀላፊዎች በቄለም ወለጋ ዞን የትምህርት ልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል። የሥራ ሀላፊዎቹ በደምቢ ዶሎ ከተማ የሚገኝ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤትና የደምቢ ዶሎ መምህራን ማሰልጠኛ ኮሌጅ የመማር ማስተማር እንቅስቃሴን ተመልክተዋል። በዚሁ ጊዜ የኮሚቴው ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) የትምህርት ጥራት ችግሮችን ለመፍታት የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ መጎልበት አለበት ብለዋል። በእስካሁኑ ሂደትም መንግስት የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የተለያዩ እርምጃዎች እየወሰደ መሆኑን ጠቅሰው እነዚህ እርምጃዎች ውጤት እንዲያመጡ የትምህርት አመራሩ ሚና የላቀ ነው ብለዋል። በቄለም ወለጋ ዞንም የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎች አበረታች እንደሆኑ መመልከታቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ አንቅፋት የሆኑት የመምህራን እጥረት፤ የትምህርት ቤቶች መሰረተ ልማት አለመሟላት እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች እየተፈቱ እንዲመጡ እገዛ ይደረጋል ብለዋል።
ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል ሀገራት በትብብር መስራት ይጠበቅባቸዋል
Feb 14, 2025 49
አዲስ አበባ፤ የካቲት 6/2017(ኢዜአ)፦ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከልና የስርጭት ምጣኔውን ለመግታት በሚደረገው ጥረት ሀገራት በትብብር መስራት እንደሚጠበቅባቸው ተገለጸ። በአዲስ አበባ ከተማ ''የማካካሻ ፍትህ ለአፍሪካውያንና ዘረዓ-አፍሪካውያን'' በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሔደ የሚገኘው 46ኛው የአፍሪካ ሕብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ተጠናቋል። የአፍሪካ ኅብረት የጤና፣ የሰብዓዊ ጉዳዮችና ማኅበራዊ ልማት ኮሚሽነር ሳማቴ ሴሶማ ሚናታ የአፍሪካ ሀገራት የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን በሚመለከት ለመገናኛ ብዙሃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በአሁኑ ወቅት በቀላሉ መግታት የሚቻሉ ተላላፊ በሽታዎች ለዜጎች የጤና እክል መንስኤ መሆናቸውንም ጠቁመዋል። ኤች.አይ.ቪ/ኤድስና ሌሎች ተላላፊ በሽታዎች በማህበረሰቡ ዘንድ እየተፈጠረ ባለ መዘናጋትና በጤና ተቋማት ቸልተኝነት ምክንያት ዜጎችን ለተባባሰ የጤና እክል እና ሞት እየዳረገ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም ሀገራት ወጥነት ባለው የጤና አገልግሎትና ተደራሽነት ላይ ትኩረት ሰጥተው መስራት እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል። ተቀማጭነቱን በሩዋንዳ ኪጋሊ ያደረገው የአፍሪካ በሽታ መከላከል ኤጀንሲ አድማሱን በማስፋት በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት አገልገሎት መስጠት እንደሚገባውም ጠቁመዋል። ይህም ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከልና የስርጭት ምጣኔውን ለመግታት የሚደረገው ጥረት እንደሚያግዝ አመልክተዋል። በሌላ በኩል በአህጉሪቷ የሰላምና ደህንነት ጉዳይ ላይም እንዲሁ ባለድርሻ አካላት ትብብራቸውን ማጠናከር እንደሚጠበቅባቸው አንሰተዋል። አፍሪካ ለሰው ሰራሽና ተፈጥራዊ አደጋ ያላት ተጋላጭነት እየተስፋፋ መምጣቱን ገልጸው፤ ለዚህም መፍትሔ መስጠት ላይ ትኩረት ማድረግ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
አህጉራዊ የስነ- ተዋልዶና መሰል የጤና አገልግሎት ተደራሽነት ለማረጋገጥ ኢትዮጵያ የበኩሏን ሚና ትወጣለች- ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ
Feb 13, 2025 62
አዲስ አበባ፤ የካቲት 06/2017(ኢዜአ)፦ በአፍሪካ የስነ- ተዋልዶና መሰል የጤና አገልግሎትን ተደራሽነት ለማረጋገጥ በሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ኢትዮጵያ የበኩሏን ሚና ለመወጣት ቁርጠኛ መሆኗን የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ገለጹ። የአፍሪካን የሥነ-ተዋልዶ እና የአፍላ ወጣቶች ጤና ሂደት በዓለም አቀፍ ስታንዳርድ ልክ ለማፋጠን የጤና ፖሊሲን ትግበራ ማቀላጠፍ እና ትብብር መፍጠር የሚያስችል አህጉራዊ የውይይት መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የአፍሪካን የጤና ሉዓላዊነት እና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ለማረጋገጥ ቅድሚያ የተሰጣቸው 24 የህክምና ምርቶችን በአህጉሪቱ ማምረት የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ይፋ ሆኗል። በአፍሪካ ሕብረት የልማት ኤጀንሲ ያዘጋጀው ፍኖተ ካርታ ቀጣናዊ የህክምና ምርቶችን በቀላሉ የሚገኙና ተደራሽ በማድረግ ኢኮኖሚውን የሚያሳድግ ነው። እነዚህ ቅድሚያ የተሰጣቸው 24 የህክምና ምርቶች ለኤች አይ ቪ/ኤድስ፣ ቲቢ የወባና እና የእናቶች ጤና ምርመራ፣ ህክምናና ክትትልን የሚያገዙ ናቸው። የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር መቅደስ ዳባ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ በአፍሪካ እየጨመረ የመጣውን የወጣቶች ቁጥር የሚመጥን የጤናና ህክምና አገልግሎት መፍጠር ይገባል። በአፍሪካ የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ጨምሮ የተለያዩ በሽታዎች አደጋ ሲፈጥሩ በራሳችን አቅም ለመከላከል ተቸግረን ነበር ብለዋል። ኢትዮጵያ ባለፋት አስርት ዓመታት በሽታን በመከላከልና ህክምና አገልግሎት የእናቶችና ህፃናትን ሞት በመሰረታዊነት መቀነስ መቻሏን ገልጸዋል። የአፍሪካ አጀንዳ 2063 እና ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት በጤናው ዘርፍ በትብብር መስራት እንደሚገባም ነው የተናገሩት። ኢትዮጵያ የስነ-ተዋልዶና አፍላ ወጣቶች ጤና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ ከአፍሪካውያን ጋር በትብብር ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗን ገልጸዋል። የአፍሪካ ሕብረት ልማት ኤጀንሲ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ናርዶስ በቀለ፣ በአፍሪካ የስነ- ተዋልዶ እና ወጣቶችን ጤና ለማሻሻል የትብብርና ቁርጠኝነት እንጂ የሀብት እጥረት የለም ብለዋል። መንግሥታት የስነ- ተዋልዶ ጤናን ቀዳሚ ብሔራዊ ስትራቴጂያቸው ሊያደርጉት እንደሚገባ ገልጸው፤ መንግስታት፣ ፖሊሲ አውጭዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በመረጃ ልውውጥ ልምድ በማካፈል መተባበር እንዳለባቸው እንዲሁ። ከውጭ ጥገኝነት መላቀቅ የሚቻለው አፍሪካዊ ችግሮችን በትብብርና በቅንጅት መስራት ከሲቸፋል እንደሆነ ገልጸዋል። በመንግሥታቱ ድርጅት ረዳት ዋና ጸሀፊ እና የሥነ ህዝብ ፈንድ ፕሮግራም ዋና ዳይሬክተር ዲየን ኬታ፣ አፍሪካውያን በጋራ በመተባበር በስነ ተዋልዶ ጤና ላይ ያለውን ትርክት መቀየር አለባቸው ብለዋል። ለዚህ ደግሞ የመንግሥቱ ድርጅት የስነ- ህዝብ ፈንድ ፕሮግራም አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑዋን ገልፀዋል።
ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል ሀገራት በትብብር መስራት እንደሚጠበቅባቸው ተገለጸ
Feb 13, 2025 53
አዲስ አበባ፤ የካቲት 6/2017(ኢዜአ)፦ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከልና የስርጭት ምጣኔውን ለመግታት በሚደረገው ጥረት ሀገራት በትብብር መስራት እንደሚጠበቅባቸው ተገለጸ። በአዲስ አበባ ከተማ ''የማካካሻ ፍትህ ለአፍሪካውያንና ዘረዓ-አፍሪካውያን'' በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሔደ የሚገኘው 46ኛው የአፍሪካ ሕብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ዛሬ አጠናቋል። የአፍሪካ ኅብረት የጤና፣ የሰብዓዊ ጉዳዮችና ማኅበራዊ ልማት ኮሚሽነር ሳማቴ ሴሶማ ሚናታ የአፍሪካ ሀገራት የጤና አገልግሎት ተደራሽነት በሚመለከት ለመገናኛ ብዙሃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በአሁኑ ወቅት በቀላሉ መግታት የሚቻሉ ተላላፊ በሽታዎች ለዜጎች የጤና እክል መንስኤ መሆናቸውንም ጠቁመዋል። ኤች.አይ.ቪ/ኤድስና ሌሎች ተላላፊ በሽታዎች በማህበረሰቡ ዘንድ እየተፈጠረ ባለ መዘናጋትና በጤና ተቋማት ቸልተኝነት ምክንያት ዜጎችን ለተባባሰ የጤና እክል እና ሞት እየዳረገ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም ሀገራት ወጥነት ባለው የጤና አገልግሎትና ተደራሽነት ላይ ትኩረት ሰጥተው መስራት እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል። ተቀማጭነቱን በሩዋንዳ ኪጋሊ ያደረገው የአፍሪካ በሽታ መከላከል ኤጀንሲ አድማሱን በማስፋት በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት አገልግሎት መስጠት እንደሚገባውም ጠቁመዋል። ይህም ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከልና የስርጭት ምጣኔውን ለመግታት የሚደረገው ጥረት እንደሚያግዝ አመልክተዋል። በሌላ በኩል በአህጉሪቷ የሰላምና ደህንነት ጉዳይ ላይም እንዲሁ ባለድርሻ አካላት ትብብራቸውን ማጠናከር እንደሚጠበቅባቸው አንሰተዋል። አፍሪካ ለሰው ሰራሽና ተፈጥራዊ አደጋ ያላት ተጋላጭነት እየተስፋፋ መምጣቱን ገልጸው፤ ለዚህም መፍትሔ መስጠት ላይ ትኩረት ማድረግ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
አህጉራዊ የስነ- ተዋልዶና መሰል የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ኢትዮጵያ የበኩሏን ሚና ትወጣለች- ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ
Feb 13, 2025 54
አዲስ አበባ፤ የካቲት 6/2017(ኢዜአ)፦ በአፍሪካ የስነ- ተዋልዶና መሰል የጤና አገልግሎትን ተደራሽነት ለማረጋገጥ በሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ኢትዮጵያ የበኩሏን ሚና ለመወጣት ቁርጠኛ መሆኗን የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ገለጹ። የአፍሪካን የሥነ-ተዋልዶ እና የአፍላ ወጣቶች ጤና ሂደት በዓለም አቀፍ ስታንዳርድ ልክ ለማፋጠን የጤና ፖሊሲን ትግበራ ማቀላጠፍ እና ትብብር መፍጠር የሚያስችል አህጉራዊ የውይይት መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የአፍሪካን የጤና ሉዓላዊነት እና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ለማረጋገጥ ቅድሚያ የተሰጣቸው 24 የህክምና ምርቶችን በአህጉሪቱ ማምረት የሚያስችል ፍኖተ ካርታ ይፋ ሆኗል። በአፍሪካ ሕብረት የልማት ኤጀንሲ ያዘጋጀው ፍኖተ ካርታ ቀጣናዊ የህክምና ምርቶችን በቀላሉ የሚገኙና ተደራሽ በማድረግ ኢኮኖሚውን የሚያሳድግ ነው። እነዚህ ቅድሚያ የተሰጣቸው 24 የህክምና ምርቶች ለኤች አይ ቪ/ኤድስ፣ ቲቢ የወባና እና የእናቶች ጤና ምርመራ፣ ህክምናና ክትትልን የሚያግዙ ናቸው። የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር መቅደስ ዳባ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ በአፍሪካ እየጨመረ የመጣውን የወጣቶች ቁጥር የሚመጥን የጤናና ህክምና አገልግሎት መፍጠር ይገባል። በአፍሪካ የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ጨምሮ የተለያዩ በሽታዎች አደጋ ሲፈጥሩ በራሳችን አቅም ለመከላከል ተቸግረን ነበር ብለዋል። ኢትዮጵያ ባለፋት አስርት ዓመታት በሽታን በመከላከልና ህክምና አገልግሎት የእናቶችና ህፃናትን ሞት በመሰረታዊነት መቀነስ መቻሏን ገልጸዋል። የአፍሪካ አጀንዳ 2063 እና ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት በጤናው ዘርፍ በትብብር መስራት እንደሚገባም ነው የተናገሩት። ኢትዮጵያ የስነ-ተዋልዶና አፍላ ወጣቶች ጤና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ ከአፍሪካውያን ጋር በትብብር ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗን ገልጸዋል። የአፍሪካ ሕብረት ልማት ኤጀንሲ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ናርዶስ በቀለ፣ በአፍሪካ የስነ- ተዋልዶ እና ወጣቶችን ጤና ለማሻሻል የትብብርና ቁርጠኝነት እንጂ የሀብት እጥረት የለም ብለዋል። መንግሥታት የስነ- ተዋልዶ ጤናን ቀዳሚ ብሔራዊ ስትራቴጂያቸው ሊያደርጉት እንደሚገባ ገልጸው፤ መንግስታት፣ ፖሊሲ አውጭዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በመረጃ ልውውጥ ልምድ በማካፈል መተባበር እንዳለባቸው እንዲሁ። ከውጭ ጥገኝነት መላቀቅ የሚቻለው አፍሪካዊ ችግሮችን በትብብርና በቅንጅት መስራት ሲቻል እንደሆነ ገልጸዋል። በመንግሥታቱ ድርጅት ረዳት ዋና ጸሀፊ እና የሥነ ህዝብ ፈንድ ፕሮግራም ዋና ዳይሬክተር ዲየን ኬታ፣ አፍሪካውያን በጋራ በመተባበር በስነ ተዋልዶ ጤና ላይ ያለውን ትርክት መቀየር አለባቸው ብለዋል። ለዚህ ደግሞ የመንግሥቱ ድርጅት የስነ- ህዝብ ፈንድ ፕሮግራም አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን ገልፀዋል።