ቀጥታ፡
ማህበራዊ
ሀገርን የማልማት ሥራ በበዓልና በእረፍት ቀናት ሳይገታ ተጠናክሮ ይቀጥላል 
Apr 12, 2026 690
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 4/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገርን የማልማት ሥራ በበዓልና በእረፍት ቀናት ሳይገታ ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ እየተገነባ በሚገኘው የኢንዱስትሪ ክላስተር የሥራ ቦታ በመገኘት በግንባታው ላይ ለሚሳተፉ ሠራተኞች ማዕድ አጋርተዋል።   ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ጊዜ፤ በተለወጠ የሥራ ባሕል በርካታ መሠረተ ልማቶች በጥራት እየተገነቡ መሆኑን ተናግረዋል። እየሰራን ሀገርን እየገነባን በዓልን እናከብራለን ያሉት ከንቲባዋ መስራት የሚያስከብር ተግባር መሆኑንና ከድህነት ለመውጣት በበዓል፣ በእረፍትም ሆነ በሌሊት ጠንክሮ መስራት የግድ እንደሚል አስገንዝበዋል። ይህ የኢንዱስትሪ ክላስተር ፕሮጀክት በአሁኑ ወቅት ለ13 ሺህ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል። ግንባታውን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ ሠራተኞች የበዓል ቀናትን ጨምሮ በከፍተኛ ተነሳሽነት እየሰሩ መሆኑንም አክለዋል።   በዓል ምሉዕ የሚሆነው ከለውጥና ከብልፅግና ጋር ሲያያዝ ነው ያሉት ከንቲባዋ፤ የማዕከሉ የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ በአሁኑ ወቅት በመጠናቀቅ ላይ እንዳለ ገልጸዋል። ግንባታው ተጠናቆ ማዕከሉ ሥራ ሲጀምር ለበርካታ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ለውጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል። ሠራተኞቹ በበዓላትም ሆነ በእረፍት ቀናት ሳይወሰኑ ሀገርን ለማልማት እያሳዩ ላለው ትጋት ምስጋና አቅርበዋል። በግንባታው ላይ እየተሳተፉ ያሉት ሠራተኞች በሰጡት አስተያየት የተደረገላቸው የማዕድ ማጋራት የሥራ ተነሳሽነታቸውን እንደሚጨምረውና ለሀገር ግንባታ ያላቸውን ቁርጠኝነት እንደሚያጠናክረው ገልጸዋል። እንዲህ ያሉ የቅርብ ክትትልና ድጋፎች ፕሮጀክቱ በተቀመጠለት የጊዜ ገደብና ጥራት እንዲጠናቀቅ ትልቅ አቅም እንደሚሆኑም ተናግረዋል።
በዓላት ሲከበሩ የታመሙትን በመጠየቅ፣ የተቸገሩትን በመርዳትና አብሮነትን በማሳየት ሊሆን ይገባል
Apr 12, 2026 111
ባሕር ዳር፤ሚያዚያ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በዓላት ሲከበሩ የታመሙትን በመጠየቅ፣ የተቸገሩትን በመርዳትና አብሮነትን በማሳየት ሊሆን ይገባል ሲሉ የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ኀላፊ አብዱልከሪም መንግሥቱ ተናገሩ። የአማራ ክልል የተለያዩ ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች ባህር ዳር በፈለገ ሕይወት አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በመገኘት ታማሚዎችን በመጠየቅ ለታካሚዎች እና አስታማሚዎች ማዕድ አጋሩ።   በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ኀላፊ አብዱልከሪም መንግሥቱ፤ ሆስፒታሉ የተሻሻለ እና ዘመናዊ የህክምና አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። የህክምና አገልግሎቱ እንዳለ ሆኖ በተለይም በዓላትን ስናከብር ታማሚዎችን አስታውሶ መጠየቅና አብሮነትን ማሳየት ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም በዓላት ሲከበሩ የታመሙትን በመጠየቅ፣ የተቸገሩትን በመርዳትና አብሮነትን በማሳየት ሊሆን ይገባል ብለዋል። የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ በሆስፒታሉ በመገኘት የታመሙትን መጠየቃቸውንና ማእድ ማጋራታቸውን ተናግረዋል። የፈለገ ሕይወት አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ሥራ አሥኪያጅ ዐቢይ ፍሰሐ በበኩላቸው፤ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች የፋሲካ በዓልን ምክንያት በማድረግ በሆስፒታሉ በመገኘት በመጠየቅና ማእድ በማጋራት አብሮነታቸውን በማሳየታቸው አመስግነዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊና የሆስፒታሉ ቦርድ ሰብሳቢ ፍሰሐ ደሳለኝ፤ የበዓላት አከባበር በተለይም ማህበራዊ እሴቱ አብሮነት፣ መረዳዳትና መተጋገዝን መሰረት ያደረገ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም የትንሳኤ በዓልን ስናከብር የተቸገሩ ወገኖችን በመርዳትና የታመሙትን በመጠየቅ መሆን ይኖርበታል ብለዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ የትንሣኤን በዓል ምክንያት በማድረግ 27ኛውን የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከል ሥራ አስጀመሩ   
Apr 12, 2026 560
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 4/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የትንሣኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ 27ኛውን የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከል በጉለሌ ክፍለ ከተማ በይፋ መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት፤ በአዲስ አበባ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ያስቻሉ ግዙፍ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን ገልጸዋል።   ሰው ተኮር ፕሮጀክቶችንም በጥራትና በፍጥነት በመገንባት በማህበራዊ ችግር ተጋላጭ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ለአብነትም የመዲናዋ የምገባ ማዕከላት እጅ አጠር ዜጎች ማህበራዊ ድጋፍ የሚያገኙበትን ወሳኝ ዕድል በመፍጠር ከፍተኛ ጠቀሜታ እያበረከቱ እንደሚገኝ አንስተዋል።   27ኛው የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከል በጉለሌ ሶስተኛው ቅርንጫፍ መሆኑን ገልጸው፤ማዕከሉ በርካታ አቅመ ደካማ ወገኖች በቀን አንድ ጊዜ የምግብ አገልግሎት የሚያገኙበትን ዕድል እንደሚፈጥር ጠቅሰዋል። በአዲስ አበባ የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከል ግንባታ ስኬት ከፍተኛ ድጋፍ እያደረጉ ለሚገኙ ባለሃብቶችና በጎ አድራጊዎችም ምስጋና አቅርበዋል። በቀጣይም የዜጎች የመረዳዳትና መደጋገፍ እሴት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ መልዕክት አስተላልፈዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምገባ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ፀዳለች ሚካኤል በበኩላቸው ፤ በምገባ ማዕከላት የሚከናወነው የምገባ መርሐ ግብር በበዓላት ወቅት ብቻ ሳይሆን በቋሚነት የሚከናወን በመሆኑ ለብዙዎች የሕይወት ተስፋ እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል።   አስተያየታቸውን የሰጡ የማዕከሉ ተጠቃሚዎች በበኩላቸው፤ ከከንቲባዋ ጋር በዓልን በማሳለፋቸው መደሰታቸውን ገልፀው ማዕከሉ አረጋውያንና ሕፃናት የእለት ጉርሳቸውን አጥተው እንዳይቸገሩ ትልቅ እፎይታ የሚፈጥርላቸው መሆኑን ተናግረዋል።
የተለያዩ ሀገራት ኤምባሲዎች ለትንሳኤ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ
Apr 12, 2026 472
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 4/2018 (ኢዜአ)፦ተቀማጭታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሀገራት ኤምባሲዎች እና አምባሳደሮች ለትንሳኤ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። በኢትዮጵያ የሩሲያ ኤምባሲ ለትንሳኤ በዓል እንኳን አደረሳችሁ በማለት በዓሉ የሰላም፣ የፍቅር እና የደስታ እንዲሆን ተመኝቷል። በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኧርቪን ማሲንጋ የትንሳኤ በዓልን ለሚያከብሩ ኢትዮጵያውያን በሙሉ ልባዊ የመልካም ምኞት መግለጫዬን አስተላልፋለሁ ሲሉ ገልጸዋል። በጾሙ ወቅት የሚታየው ጽናትና የኢትዮጵያ ውብ እሴቶች፣ የኢትዮጵያውያንን ጥልቅ እምነትና የበለጸገ የባህል ማንነት በግልጽ የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል። የትንሣኤ በዓል የታደሰ ሕይወትን፣ ተስፋንና በረከትን ይዞ እንዲመጣ ተመኝተዋል። በኢትዮጵያ ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለትንሳኤ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ያለው ደግሞ በኢትዮጵያ የእስራኤል ኤምባሲ ነው። በዓሉ የሰላም እና የፍቅር እንዲሆን ተመኝቷል። በኢትዮጵያ የአውስትራሊያ አምባሳደር ፒተር ሀንተር (ዶ/ር) የትንሳኤ በዓል የደስታ እና የሀሴት እንዲሆን ተመኝተዋል። በኢትዮጵያ የዩናይትድ ኪንግደም ኤምባሲ የትንሳኤ በዓል የተስፋ፣የእድሳት እና የአብሮነት ጊዜ መሆኑን አመልክቷል። በዓሉ የሰላም፣የፍቅር እና የደስታ እንዲሆን መልካም ምኞቱን ገልጿል። በኢትዮጵያ የኢራን ኤምባሲ እንኳን ለትንሳኤ በዓል አደረሳችሁ ሲል የመልካም ምኞት መግለጫውን አስተላልፏል። በኢትዮጵያ የፓኪስታን ኤምባሲ የትንሳኤ በዓል የደስታ እና የበረከት እንዲሆን ተመኝቷል። ስዊድን፣ ስዊዘርላንድ፣ ጀርመን፣ አርሜኒያ፣ እና ካናዳ ሌሎች ለትንሳኤ በዓል መልካም ምኞታቸውን ከገለጹ ኤምባሲዎች መካከል ይጠቀሳሉ። በተያያዘም የተባበሩት መንግግስታት ድርጅት የኢትዮጵያ ቢሮ ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች እንኳን ለትንሳኤ በዓል በሰላም አደረሳችሁ ሲል መልካም ምኞቱን ገልጿል። የትንሳኤው ወቅት የተስፋ፣የመታደስና የአብሮነት እንዲሆንም ተመኝቷል።
የገንዳ ውኃ ከተማ ወጣቶች በዓሉን አብሮነትን በሚያጠናክር መልኩ እያከበሩ ነው
Apr 12, 2026 237
ገንዳ ውኃ፤ሚያዚያ 4/2018 (ኢዜአ)፡- የትንሳኤ በዓልን አቅመ ደካማ ወገኖች በማሰብና አብሮነትን በሚያጠናክር መልኩ እያከበሩ መሆናቸውን የገንዳ ውኃ ከተማ ወጣቶች ገለጹ። ወጣቶቹ የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ ለአቅመ ደካሞች፣ ለአረጋውያንና ለተቸገሩ የህብረተሰብ ክፍሎች የቅርጫ ሥጋ አከፋፍለዋል። ​​ከድጋፍ አድራጊ ወጣቶች መካከል ኤልያስ ጋሻው እንደገለጸው የማዕድ የማጋራቱ ተግባር ላለፉት ዓመታት ተጠናከሮ ቀጥሏል።   በዚህም ጧሪና ደጋፊ የሌላቸው አረጋውያን፣ አሳዳጊ የሌላቸው ሕፃናትና ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ማድርጋቸውን ገልጸዋል። በዛሬው እለትም ወጣቶች ከራሳቸው ባዋጡት እንዲሁም ከህብረተሰቡና ከተቋማት ባሰባሰቡት ገንዘብ የእርድ እንስሳት ገዝተው የቅርጫ ሥጋ ማከፋፈላቸውን የገለጸው፣ ይህ መልካም ተግባር የአዕምሮ እርካታ ይሰጣል ብሏል። የከተማው ወጣቶች በዓልን የሌላቸውን ወገኖች በማሰብና አብሮነትን በሚያጠናክር መልኩ የማክበሩ ባህል እንደሚያጠናክርም ተናግሯል።   ሌላኛው ተሳታፊ ወጣት ሲሳይ አለበል በበኩሉ፤ በዓልን ከራስ ባለፈ ለሌላቸው ወገኖች በማካፈል በአብሮነት ማክበር ውስጣዊ እርካታን ያጎናጽፋል ብሏል። በየበዓላቱ የሚያደርጉትን በጎ ተግባር በቀጣይም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጧል። የገንዳ ውኃ ከተማ አስተዳደር ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ተስፋ መኮንን እንዳሉት፤ የወጣቶች በጎ ፈቃድ አገልግሎት ብዙ ወገኖችን ከሀሳብ የታደገ አርአያነት ያለው ተግባር ነው።   ​በማዕድ ማጋራቱ 322 ወገኖች ድጋፍ እንደተደረገላቸው ገልጸው፣ በቅን አሳቢ ወጣቶች የሚከናወኑ በጎ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። ​በማዕድ ማጋራት ድጋፍ ከተደረገላቸው ወገኖች መካከል ወይዘሮ የሻረግ አስማረ በሰጡት አስተያየት በዓሉን ተደስተው እንዲያሳልፉ ድጋፍ ያደረጉላቸውን ወጣቶችና የተሳተፉ አካላትን አመስግነዋል። በአቅም ማነስ ምክንያት ለበዓሉ ምንም ዝግጅት ሳያደርጉ ባዶ ቤት ተቀምጠው እንደነበር የገለጹት ወይዘሮዋ፣ በበዓል ወቅት የሚደረግ የእርስ በርስ መደጋገፍ አብሮነትን እንደሚያጠናክር ገልጸዋል።
የትንሳኤ በዓል በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ እየተከበረ ነው
Apr 12, 2026 537
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 4/2018 (ኢዜአ)፡- የትንሳኤ በዓል በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ይገኛል። በዓሉ ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ የተነሳበት ዕለት የሚታወስበት ነው። የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ የኃይማኖት አባቶች ባስተላለፉት መልዕክት ሕዝበ ክርስቲያኑ የትንሳኤን በዓል የአንድነትና የቸርነት እሴቶችን በማጎልበት፣ በመረዳዳትና በአብሮነት እንዲያሳልፍ አባታዊ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። ሕዝበ ክርስቲያኑ ከቂም በቀልና ከጥላቻ በመራቅ፣ ከሌሎች ወንድምና እህቶቻቸው ጋር በመተባበር ለሀገር ሰላምና ፍቅር መስራት እንዳለበት አመልክተዋል። የሃይማኖት አባቶቹ በመልዕክታቸው ማጠቃለያ ላይ በዓሉ የሰላም፣ የፍቅርና የደስታ እንዲሆን ለሁሉም የክርስትና እምነት ተከታዮች መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል። የትንሳኤ በዓል በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በተለያዩ ዝግጅቶች በመላው ኢትዮጵያ እየተከበረ ይገኛል።
የሀገር ባለውለታን መንከባከብ የሁሉም ዜጋ ኃላፊነት ነው 
Apr 12, 2026 222
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 4/2018 (ኢዜአ)፡-የሀገር ባለውለታ አረጋዊያንን መንከባከብ የሁሉም ዜጋ ኃላፊነት መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ወይዘሮ ቡዜና አልከድር ገለጹ። የ2018 ዓ.ም የትንሣኤ በዓል በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በታላቅ ድምቀት እየተከበረ ይገኛል። በዓሉን በማስመልከትም የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ወይዘሮ ቡዜና አልከድር የወደቁትን አንሱ አረጋዊያን መርጃ ማዕከል ለሚገኙ አረጋዊያን ማዕድ አጋርተዋል።   በዚሁ ወቅትም ኢትዮጵያዊያን በዓላትን ሲያከብሩ የተቸገሩና አቅመ ደካማ ወገኖችን በማሰብ ሊያሳልፉ እንደሚገባ መልዕክት አስተላልፈዋል። በበዓላት ወቅት ያለው ከሌለው ጋር በአብሮነትና መረዳዳት ማሳለፍም የኢትዮጵያዊያን የቆየ እሴት መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የሀገር ባለውለታ አረጋዊያንን የመንከባከብ ሥራ የሁሉም ዜጋ የሞራል ግዴታ መሆኑን አስገንዝበዋል። የመዲናዋ ነዋሪዎችም አቅመ ደካማ ወገኖችን በማሰብ በመረዳዳትና መተሳሰብ ሊያሳልፉ እንደሚገባ ገልጸዋል።   የወደቁትን አንሱ አረጋዊያን መርጃ ማዕከል የሚጦሩ አረጋዊያን በበኩላቸው፤ በማዕድ ማጋራት መርሃ ግብሩ የወገናቸውን አስታዋሽነት በተግባር ያዩበት መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም በማዕከሉ ተገኝተው የማዕድ ማጋራት የድጋፍ መርሃ ግብር ላደረጉላቸው ሁሉ ምስጋና አቅርበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ለትንሳኤ በዓል ማዕድ አጋሩ
Apr 12, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 4/2018 (ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው የትንሳኤ በዓልን በማስመልከት ለተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች በአንድነት ፓርክ ማዕድ አጋርተዋል።   በመላው ኢትዮጵያ በክርስትና ጥላ ውስጥ በሚገኙ ቤተ-እምነቶች ያሉ ክርስቲያኖች የትንሳኤን በዓል በተስፋ፣ በመስዋዕትነት እና በአዲስ መነሳት መንፈስ በአንድነት እያከበሩ እንደሚገኙ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። ከሳምንታት የፆም፣ ጥሞና እና ራስን የመመልከት ጊዜ በኋላ ፋሲካ በእውነተኛ አምልኮ፣ መንፈስን አድሶ፣ ቤቶችንም በደስታ የሚሞላ መሆኑንና በዘመድ አዝማድ መጠያየቅ እንዲሁም ማዕድ መካፈል ፍቅርን የሚያዳብርበት መሆኑን ገልጿል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ዓመታዊውን የፋሲካ የመዐድ ማጋራት ከተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጋር በአንድነት ፓርክ በጋራ መታደማቸውን የጠቀሰው ጽህፈት ቤቱ፤ ይህም ለእውነተኛው የአንድነት መንፈስ ጉልህ ማሳያ መሆኑን አመልክቷል። በዓለ ትንሳኤው በመላው ኢትዮጵያ የእምነት፣ ቤተሰባዊነት እና የመታደስ መንፈስ የሚታይበት ጊዜ መሆኑን በመጥቀስ፤ ሁላችንም በዚህ የትንሳኤ መንፈስ ዛሬም፣ ነገም፣ ሰርክ ቤታችንንና ልባችንን ለተቸገሩ ወገኖች እንድንከፍት የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ጥሪውን በማስተላለፍ መልካም በዓል ተመኝቷል።
ባሳለፍነው ሳምንት …
Apr 11, 2026 138
ከመጋቢት 27 እስከ ሚያዝያ 3 ቀን 2018 ዓ.ም ከተከናወኑ ዐበይት ጉዳዮች መካከል ፦ • ለትንሣኤ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክቶች ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) ባስተላለፉት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት፤ የትንሣኤ በዓል በክርስቲያኖች ዘንድ ልዩ ቦታ ያለው በዓል ነው፤ ሞት የተሻረበትና ሕይወት ዋስትና ያገኘበት ነው ብለዋል። የትንሣኤ በዓል ከሞት ባሻገር ሕይወት ከመቃብር ባሻገር ትንሣኤ መኖሩ የታወጀበት መሆኑንም ገልፀው፤ ሞት መጨረሻ መቃብር መዳረሻ አለመሆናቸው የተረጋገጠበት ነው ብለዋል በመልዕክታቸው። የዘንድሮውን ትንሣኤ የምናከብረው ሀገራችን ኢትዮጵያ በሚያልፍ ፈተና ውስጥ እንዳለች እያሰብን ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ መንገዳችን ረጅም፣ ጉዟችን ፈታኝ መሆኑን እናውቃለን ሲሉ ገልፀዋል። ብርሃን እንዳናይ የሚጋርዱ በጥልቁ ጨለማ ጠፍተን እንድንቀር አሥረው ለመያዝ የሚሞክሩ ወጥመዶች ብዙ ናቸው፤ ወደ ተስፋ ምድር እንዳንሻገር የሚጎትቱ ሰበቦች ሞልተዋል፤ ዳሩ ግን ከሕማማቱ ወዲያ ትንሣኤ ከዕንቅፋቱ ባሻገር ስኬት እንደሚጠብቀን አምነን እንታገላለን ሲሉም አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ ወደ ትንሣኤ መቃረቧን ገልፀው፤ የኢትዮጵያ ትንሣኤ ከሚበሰርባቸው ምዕራፎች አንዱ ግንቦት ላይ የሚካሄደው ምርጫ መሆኑንም አመላክተዋል። ትንሣኤን ያለ ሕማማት እንደማናስበው ሁሉ ዴሞክራሲንም ከውጣ ውረድ ነጥሎ ማየት አይቻልም ብለዋል። • የቡሩንዲው ፕሬዚዳንት በኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለሁለት ቀናት በኢትዮጵያ ጉብኝት ካደረጉት የቡሩንዲው ፕሬዚዳንት ኢቫሪስቴ ንድያይሺሚዬ ጋር ውጤታማ የሁለትዮሽ ውይይት ማድረጋቸውን ባሳለፍነው ሳምንት ገልጸዋል። በዚሁ ወቅትም በተለያዩ ዘርፎች ያለንን ትብብር ለማጠናከር ያለሙ በርካታ የመግባቢያ ሰነዶች ፊርማ አከናውነናል ሲሉም አስታውቀዋል። ስምምነቶቹ ለሁለቱም ሀገራት የበለጸገ እና የተባበረ መጻኢ ዕድልን የሚያረጋግጡ የቆዩ ግንኙነቶቻችንን ወደ ተጨባጭ ትብብር ለመቀየር እንደ ወሳኝ መሠረት የሚያገለግሉ የጋራ ቁርጠኝነታችን ማሳያ ጭምር ናቸው ብለዋል። ጉብኝታቸውን እንዳጠናቀቁም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተገኝተው ሸኝተዋቸዋል። • ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) ባሳለፍነው ሳምንት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከአፍሪኤግዚም ባንክ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ኢሎምቢ (ዶ/ር) ጋር ተወያይተዋል። በዚሁ ወቅትም ስትራቴጂካዊ ግንኙነታችንን በምናጠናክርባቸው ጉዳዮች ዙሪያ መክረናል ብለዋል። • የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አሥተዳደር ዓመታዊ አፈጻጸም ግምገማ ባሳላፍነው ማክሰኞ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አሥተዳደር ፕሬዚዳንት ሌፍተናንት ጄኔራል ታደሰ ወረደ ዓመታዊ የአፈፃፀም ሪፖርት ቀርቦላቸው በውጤቶቹ ላይ ግምገማ እና ውይይት አድርገዋል። • የሌፍተናንት ጄኔራል ታደሰ ወረደ ሹመት መራዘም በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ መንግሥት አንቀፅ 62(9) እና በዐዋጅ ቁጥር 359/1995 አንቀጽ 14 ንዑስ አንቀፅ 2(ለ) መሠረት የትግራይ ክልል አካታች ጊዜያዊ አሥተዳደርን በርዕሰ መሥተዳደርነት እንዲመሩ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የትግራይ ክልል አካታች ጊዜያዊ አሥተዳደር አስመልክቶ በጸደቀው ደንብ ቁጥር 479/2013 አንቀጽ 4(2) እና የዓመቱን የሥራ አፈጻጸም ባቀረቡት መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የሌፍተናንት ጄኔራል ታደሰ ወረደን ሹመት ለአንድ ዓመት አራዝመዋል። • ማዕድ ማጋራት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መጪውን የፋሲካ በዓል ምክንያት በማድረግ ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሠራተኞች እና ጽሕፈት ቤቱ ለሚያሳድጋቸው ሕጻናት ማዕድ አጋርተዋል። • የአምባሳደር ቆንጂት ሥነ ጊዮርጊስ ኅልፈተ ሕይወት አምባሳደር ቆንጅት፤ በዲፕሎማሲው መስክ ለኢትዮጵያና ለአፍሪካ ላበረከቱት ጉልኅ አስተዋጽዖ፣ ለሰጡት አስተምኅሮና ለነበራቸው ብልኅ አመራር ምንጊዜም ሲታወሱ እንደሚኖሩ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ ባስተላለፉት የኀዘን መግለጫ መልዕክት ገልጸዋል። ትጉኅና ከብረት የጠነከሩ ዲፕሎማት ነበሩ በማለት ለሙያቸው የነበራቸውን ጽኑ አቋምና የሀገር ፍቅር ስሜትም አንስተዋል። ከግማሽ ክፍለ ዘመን በላይ ኢትዮጵያን በዲፕሎማሲው መስክ ያገለገሉት አምባሳደር ቆንጂት በማረፋቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተሰማቸውን ኀዘን ገልጸዋል። አምባሳደሯ ለሕግ፣ ለአሠራር፣ ለፕሮቶኮል እና ለኢትዮጵያ ጥቅሞች በነበራቸው የጸና አቋም እናስታውሳቸዋለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ከእርሳቸው በኋላ አያሌ ሴት ዲፕሎማቶች በመስኩ እንዲሠማሩ መንገዱን አስፍተዋል ብለዋል። በተመሳሳይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ባስተላለፉት የኀዘን መግለጫ መልዕክት፤ በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ታሪክ ውስጥ የማይረሳ እና ታላቅ ዐሻራን ማሳረፍ የቻሉት አምባሳደር ቆንጂት ሥነ ጊዮርጊስ ከዚህ ዓለም በሞት በመለየታቸው ጥልቅ ኀዘን ተሰምቶኛል ብለዋል። አምባሳደር ቆንጂት እስከ ከፍተኛ ዲፕሎማትነት በደረሰ ረጅም የሥራ ዘመናቸው ለሀገራችን ብሔራዊ ጥቅም ያስመዘገቡት ድል እና ያበረከቱት አስተዋጽዖ ሁልጊዜም በክብር የሚታወስ ነው ሲሉ ገልጸዋል። ባሳለፍነው ሳምንት “ፖሊሳዊ አንድነት ለዘላቂ ሰላም” በሚል መሪ ሐሳብ 20ኛው የፖሊስ ኮሚሽነሮች መክፈቻ ጉባዔ ተካሂዷል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በዚሁ ወቅት፤ የመደመር መንግሥት የኢትዮጵያ ፖሊስ በሚሰጠው አገልግሎት ታማኝም አሳማኝም መሆን አለበት ብሎ ያምናል ብለዋል። የፖሊስ ኃይላችን የጥፋት ኃይሎች በሀገራችንና በሕዝባችን ላይ የሰነዘሩትን ጥቃት በአንድነት በመቆምና መስዋዕትነት በመክፈል ቀልብሷል፤ ይህም ለሁላችንም ኩራት ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የፖሊስ አመራሮችና የሠራዊቱ አባላት በዕውቀት፣ በታማኝነትና በሕዝብ አገልጋይነት ሥነ-ልቦና ለላቀ ተልዕኮ እንድትዘጋጁ አደራ እላለሁ ብለዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ለትንሣኤ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ
Apr 11, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 3/2018 (ኢዜአ)፦‎ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ለኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፣ የትንሣኤ በዓል አራት ዋና ዋና ነገሮች ማለትም ሞት፣ መግነዝ፣ መቃብር እና ማኅተም የተሻሩበት ታላቅ ዕለት መሆኑን ገልጸዋል። ሞትና መቃብር ከአዳም የመጡ የሰው ልጅ ዕዳዎች መሆናቸውን ጠቅሰው፣ መግነዝ በወዳጅ፣ ማኅተም ደግሞ በጠላት የሚደረጉ ተግዳሮቶች እንደሆኑ አስረድተዋል። ሰው በአራቱም ፈተናዎች እንደሚገጥመውና ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የአዳምን የሞትና የመቃብር ዕዳ፣ የነዮሴፍን መግነዝ እንዲሁም የነቀያፋን ማኅተም ሽሮ ትንሣኤውን ማወጁን አብራርተዋል። ኢትዮጵያም ያለፈ ዘመን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ማኅበራዊ ዕዳ እንዳለባት ያነሱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ እነዚህን ችግሮች መሻር ሲያቅታቸው ወዳጆች ያለበሱንን የፖሊሲና የስትራቴጂ መግነዝ እንዲሁም ጠላቶች ከዕዳ እንዳንወጣ ያተሙብንን ማኅተም እንሰብራለን ብለዋል። ሀገራዊ ዕዳዎችን በሀገራዊ ምክክር፣ በሽግግር ፍትሕ እና በተሐድሶ ፕሮግራሞች ለመሻር መንግሥት እየሠራ መሆኑን የገለጹት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ መግነዝ የተባሉትን የፖሊሲ ችግሮች በሪፎርሞች እንደሚያቃልሉና የተዘጋብንን በር በመክፈት ማኅተሙን እንደሚመክን አስታውቀዋል። የትንሣኤ ብርሃን በእኩለ ሌሊት እንደመጣ በማስታወስ፣ የሀገሪቱ ትንሣኤም ለነቁና ለተዘጋጁ ዜጎች የሚታይ መሆኑን ጠቁመዋል። ሌሊታችን የመጣ ለመሰላቸው ሁሉ፤ ለእኛ ግን ትንሣኤያችን መሆኑን እናውጃለን በማለት መላው ኢትዮጵያውያን በዓሉን በንቃትና በተስፋ እንዲያከብሩ መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
ትንሳኤን የመሰሉ በዓላት የመደጋገፍና የአብሮነት እሴቶቻችንን አጠናክረን የምናስቀጥልባቸው ሊሆኑ ይገባል
Apr 11, 2026 99
መቱ ፤ሚያዝያ 3/2018 (ኢዜአ):- ትንሳኤን የመሰሉ ሃይማኖታዊ በዓላት የሕብረተሰቡን የኖረ የመደጋገፍና የአብሮነት እሴቶችን አጠናክረን የምናስቀጥልባቸው ሊሆኑ እንደሚገባ ተገለጸ። የመቱ ከተማ አስተዳደር የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ 240 ለሚሆኑ አቅመ ደካማ ወገኖች ማዕድ የማጋራት መርሃ ግብር አከናውኗል። በወቅቱም የከተማዋ ከንቲባ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ካሳሁን ጉደታ እንደገለፁት፤ በማዕድ ማጋራቱ አካል ጉዳተኞችና ድጋፍ የሚሹ አረጋውያን እንዲሁም ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው የሕብረተሰብ ክፍሎች ተካተዋል። ትንሳኤን የመሰሉ በዓላት የመደጋገፍና የአብሮነት እሴቶቻችንን አጠናክረን የምናስቀጥልባቸው ሊሆኑ እንደሚገባ አመልክተዋል።   የማዕድ ማጋራትና የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባራት የሕብረተሰቡን የመረዳዳትና የአብሮነት እሴቶች እያሳደጉ መሆናቸውንም ነው አቶ ካሳሁን የገለጹት። የመቱ ከተማ ማህበራዊ ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ሀምዝያ ታምሩ በበኩላቸው በዓላት የአንድነት፣ የፍቅር፣ የመተሳሰብና የመደጋገፍ እሴቶቻችንን በማጉላት ረገድ ሚናቸው የጎላ ነው ብለዋል። የትንሳኤን በዓል ስናከብርም አብሮነታችንንና ድጋፋችንን ከሚሹ ወገኖች ጋር ሊሆን ይገባል ነው ያሉት። ማዕድ ከተጋሩት መካከል ወይዘሮ እጅጋየሁ ቶላ እና ወይዘሮ ፈጠነች በላይ ባገኙት ድጋፍ መደሰታቸውን ገልጸው ያገኙት ድጋፍ በዓሉን በደስታ ለማሳለፍ እንደሚያስችላቸው ተናግረዋል። በዓሉን በደስታ ለማሳለፍ ድጋፍ ላደረገላቸው አካልም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።  
የትንሳኤ በዓልን በመረዳዳትና ለሀገር ሰላም በመስራት ማሳለፍ ይገባል- የሃይማኖት አባቶች
Apr 11, 2026 90
ጎንደር፣ ገንዳውኃ፣ ሚያዝያ 3/2018 (ኢዜአ):- የትንሳኤ በዓልን በመረዳዳትና ለሀገር ሰላም በመስራት ማሳለፍ እንደሚገባ የሃይማኖት አባቶች አስገነዘቡ። የሃይማኖት አባቶቹ እንዳመለከቱት ህዝበ ክርስቲያኑ የትንሳኤ በዓልን በመረዳዳትና ለሀገር ሰላም በመስራት መሆን አለበት። የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ሀገረ ስብከት ሊቀ ዻዻስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ዮሐንስ ባስተላለፉት መንፈሳዊ መልእክት ምዕመኑ የትንሳኤ በዓልን ሲያከብር ሃይማኖታዊ አስተምህሮውን በመተግበር መሆን አለበት ብለዋል። በዚህም የተቸገሩ ወገኖችን በመርዳትና ለሀገር ሰላምና አንድነት በመስራት መሆን እንደሚገባውም ተናግረዋል፡፡   በጎንደር ከተማ የሃገር ሽማግሌ አባ ብርሃኑ ተስፋዬ በበኩላቸው ህዝበ ክርስቲያኑ የትንሳኤ በዓልን ሲያከብር ካለው ላይ በመቀነስ ለአቅመ ደካማ ወገኖች በማካፈል ሊሆን እንደሚገባ አመልክተዋል። በበዓሉ ወቅት ሃይማኖታዊ ግዴታ የሆነውን በጎነትና መተሳሰብ አጠናክረን መቀጠል አለብን ብለዋል።   የትንሳኤ በዓል ያለው ለሌለው የሚያካፍልበት ነው ያሉት ደግሞ ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ አድማሴ ደሞዝ ናቸው፡፡ በዓሉ አብሮነታችንን የምናጠናክርበት እንዲሁም ለአገራችን ሰላምና አንድነት የምንተጋበት መሆን እንዳለበትም መክረዋል። በተመሳሳይም የምዕራብ ጎንደር ዞን ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ አእላፍ ቆሞስ አባ ኃይለ ማርያም ያሳይ፤ በበኩላቸው ትንሳዔ ለሰው ልጆች ደህንነትና ፍቅር ሲባል ህይወት የተከፈለበት በዓል መሆኑን ገልጸዋል።   በዓሉን ስናከብርም ፍቅርን፣ ሰላምንና ትህትናን በመላበስ ለሀገር ሰላምና አንድነት አበክሮ በመስራት ሊሆን ይገባል ብለዋል። በዓሉን​ ያላቸው ለሌላቸው በማካፈልና በይቅርታ ማሳለፍ እንደሚገባም አስረድዋል። ​በዓሉን ስናከብር የተቸገሩትን በመርዳትና አብሮነትን በማጠናከር መሆን እንዳለበት የተናገሩት ደግሞ በሀገረ ስብከቱ የትምህርትና ስልጠና ክፍል ኃላፊ መጋቢ ሀይማኖት ፍሬአሚን ጌቴ ናቸው።   ምዕመኑ በዓሉን ሲያከብር ለሌሎች ሰዎች ሰላምና ደስታ የሚሰጡ ተግባራትን በመፈጸም መሆን አለበት ብለዋል።    
የትንሳዔ በዓልን ስናከብር በታላቅ ፍቅር እና መተሳሰብ ሊሆን ይገባል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 11, 2026 471
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 3/2018 (ኢዜአ)፦ የትንሳዔን ምሳሌነት መሰረት በማድረግ በታላቅ ፍቅር እና መተሳሰብ በዓሉን ማክበር እንደሚገባ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ዛሬ በትንሣኤ በዓል ዋዜማ በጎ ፈቃደኞችን በማስተባበር የተገነቡ 215 ዘመናዊ የመኖሪያ ቤቶች ከተለያዩ ክፍለ ከተሞች ለተውጣጡ አቅመ ደካሞች፣ አካል ጉዳተኞች፣ ለአገር ባለውለታዎችና ለልማት ተነሺዎች ከሙሉ የቤት ቁሳቁስና ከበዓል መዋያ ጋር በስጦታ አበርክተዋል፡፡   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት፤ የከተማ አስተዳደሩ ከህዝብ ጋር በመሆን በርካታ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። መንግስት በጎ ፈቃደኞችን በማስተባበር ያስገነባቸውን 215 ቤቶች መገንባቱን አመልክተው፤ መኖሪያ ቤቶች በተለያዩ ክፍለ ከተሞች ይኖሩ ለነበሩ አቅመ ደካሞች፣ አካል ጉዳተኞች፣ ሀገር ባለውለታዎችና ልማት ተነሺዎች ከሙሉ የቤት ቁሳቁስና ከበዓል መዋያ ጋር በስጦታ አበርክተናል ብለዋል። የበጎነት የመኖሪያ መንደር ቀደም ሲል የአንድ አባወራ ይዞታ ብቻ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ላይ ለ40 አባወራዎች የሚሆን ዘመናዊ መኖሪያ ቤት ተገንብቶበታል ነው ያሉት። ይህ የግንባታ ሂደትም ትንሽ ቦታን በአግባቡ አልቆ በጋራ የመጠቀም እሳቤን በተግባር ያሳየ መሆኑን አስገንዝበዋል። የኦሮሚያ ባንክ ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ 40 አባወራዎችን መያዝ የሚችል ባለ አራት ወለል ህንፃ በማስገንባት ማህበራዊ ኃላፊነቱን መወጣቱን ተናግረዋል። ስንተባበር ከተማችን ይዘምናል፤ ኑሮአችንም ክብራችንን የጠበቀ ይሆናል ያሉት ከንቲባ አዳነች፤ ኑሮ እና ሁለንተናዊ ዕድገት እንደሚመጣ ገልጸዋል።   በሁሉም ክፍለ ከተሞች ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን በመወጣት የመኖሪያ መንደሮችን ለዜጎች የገነቡ አካላትን አመስግነው፤ ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች ለትንሳዔ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። የኦሮሚያ ባንክ ቦርድ ሰብሳቢ አሰፋ ስሜ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ መንግስት በማከናወን ላይ ያለው አካታች እና ሰው ተኮር ልማት የሚደነቅ ነው ብለዋል። ባንኩ ከመንግስት ጋር በመተባበር ለዜጎች መኖሪያ በመገንባቱም የተሰማቸውን ደስታ ገልጸው፤ ይህን ተግባር በቀጣይም አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል።
ህዝበ ክርስቲያኑ በዓሉን ሲያከብር የተቸገሩትን በመርዳትና ጥልን በይቅርታ በመሻገር ሊሆን ይገባል--የሃይማኖት አባቶች
Apr 11, 2026 126
ዲላ፤ ሚያዝያ 3/2018 (ኢዜአ) ፡-ህዝበ ክርስቲያኑ የትንሣኤን በዓልን ሲያከብር የተቸገሩትን በመርዳት፣ ከክፉ ሥራ በመራቅና ጥልን በይቅርታ በመሻገር ሊሆን እንደሚገባ በዲላ ከተማ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የሃይማኖት አባቶች ገለጹ። የትንሣኤ በዓል ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች መዳን መከራን በመቀበል ሞትን ድል አድርጎ የተነሳበት በመሆኑ ልዩ ትርጉም ተሰጥቶ የሚከበር መሆኑን ነው የሃይማኖት አባቶቹ ያነሱት። በመሆኑም ምዕመኑ በዓሉን ሲያከብር ልዩነቶችን በማጥበብ፣ ከክፉ ሥራ በመራቅ፣ ጥልን በይቅርታ በመሻገር፣ ለሀገር ሰላምና አንድነት በጋራ በመቆም ሊሆን እንደሚገባም መልዕክት አስተላልፈዋል። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የዲላ ደብረ ገነት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ስብከተ ወንጌል ሃላፊ መጋቤ ሀዲስ ኤልያስ ብዙነህ የትንሣኤ በዓል ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች መዳን መከራን በመቀበል ሞትን ድል አድርጎ የተነሳበት መታሰቢያ እለት ነው። ከትንሳኤ የተማርነው ፍቅርንና ይቅርታን በመተግበር፣ የተቸገሩትን በመርዳትና በመተጋገዝ በዓሉን ማሳለፍ ነው ሲሉም አመልክተዋል። ትንሣኤ የፍቅርና የምህረት በዓል መሆኑን የገለፁት ደግሞ በኢትዮጵያ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን የዲላ ክርስቲያኖች ረዳት ማርያም ቁምስና ቆሞስ አባ ፍስሃየ መለስ ናቸው። ምዕመኑ በዓሉን ሲያከብር ልዩነቶችን በማጥበብ፣ ከክፉ ሥራ በመራቅ፣ ጥልን በይቅርታ በመሻገርና ለሀገር ሰላምና አንድነት በጋራ በመቆም ሊሆን እንደሚገባም ገልፀዋል። በተለይም በበዓሉ ወቅት አቅመ ደካሞችንና ረዳት የሌላቸውን ወገኖች በማሰብና ካለን ላይ በማካፈል በዓሉን በበረከት ማክበር እንደሚገባ አሳስበዋል። የዲላ የካህናት መቅደስ ቤተክርስቲያን መጋቢ ሕርባዬ ደበበ በበኩላቸው ትንሳኤ ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አደርጎ በመነሳት የሰው ልጆችን የሃጥያት እዳ የከፈለበት በመሆኑ ልዩ ትርጉም ያለውና በድምቀት የሚከበር በዓል ነው ብለዋል። ትንሳኤ አምላክ ሰው በመሆን ለሰው ልጆች ያለውን ፍቅርና ርህራሄ እንዲሁም ምህረትን ያስተማረበት መሆኑን አንስተው እኛም ከዚህ በመማር በዓሉን ስናከብር በይቅርታና በሰላም መሆን አለበት ብለዋል።  
ሕዝበ ክርስቲያኑ የትንሳኤ በዓልን በአብሮነት እና በመረዳዳት ሊያሳልፍ ይገባል - የኃይማኖት አባቶች
Apr 11, 2026 583
አዲስ አበባ ሚያዝያ 3/2018 (ኢዜአ)፦ ሕዝበ ክርስቲያኑ የትንሳኤን በዓል የአንድነትና የቸርነት እሴቶችን በማጎልበት፣ በመረዳዳትና በአብሮነት እንዲያሳፍል የኃይማኖት አባቶች ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። የኃይማኖት አባቶቹ በመልዕክታቸው፤ በዓሉ ኢትዮጵያዊ አብሮነትንና የቸርነት እሴትን በማጠናከርና የተቸገሩ ወገኖችን በመርዳት ማክበር ይገባል ብለዋል። ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘ ኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘ አክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ባስተላለፉት መልእክት፤ የትንሳኤ በዓልን ሃይማኖቱ የሚያስተምራቸውን መልካም ስራዎች በተግባር በመግለጽ ልናከበር ይገባል ብለዋል፡፡ የበዓሉ መገለጫ ዕሴት የሆነውን መልካም ስብዕና እና ቅን አስተሳሰብ መጠቀም አስፈላጊ መሆኑን አመልክተው፤ በዓለም አቀፍ ደረጃም ሆነ በሀገርም የሚያጋጥሙ ፈተናዎችን በጽናት ማለፍ እንደሚገባ ተናግረዋል። ምዕመናን በዓሉን ሲያከብሩ የተቸገሩ ወገኖችን በማሰብ እና በማገዝ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል።   የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳሳት ብፁዕ ካርዲናል አቡነ ብርሃነ ኢየሱስ በበኩላቸው፤ ምዕመናን ከፈጣሪያቸው የተማሩትን በጎ ምግባር በተግባር እንዲያሳዩ ጥሪ አቅርበዋል። ሕዝበ ክርስቲያኑ ከቂም በቀልና ከጥላቻ በመራቅ፣ ከሌሎች ወንድምና እህቶቻቸው ጋር በመተባበር ለሀገር ሰላምና ፍቅር መስራት እንዳለባቸው ገልጸዋል። በተለያዩ አካባቢዎች በችግር ውስጥ የሚገኙ ዜጎችን መርዳትና መደገፍ የበዓሉ ዋነኛ መገለጫ ሊሆን እንደሚገባም አክለው ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል ፕሬዚዳንት ቄስ ደረጀ ጀንበሩ፣ ትንሳኤ ፈጣሪ ለሰው ልጆች ያለውን ጥልቅ ፍቅር የገለጸበት በዓል መሆኑን ገልጸዋል።   ትንሳኤ ጥላቻ በፍቅር፣ መለያየት በአንድነት፣ እንዲሁም ሽንፈት በድል የተተካበት መሆኑን አመልክተው፤ በምዕመናን ዘንድ ይቅር ባይነት ሊነግስ እንደሚገባ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ልጆቿ ሰርተው የሚለወጡባት ምቹ ሀገር እንድትሆን ሁላችንም እርስ በእርስ ልንደጋገፍ ይገባል ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። የሃይማኖት አባቶቹ በመልዕክታቸው ማጠቃለያ ላይ በዓሉ የሰላም፣ የፍቅርና የደስታ እንዲሆን ለሁሉም የክርስትና እምነት ተከታዮች መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ
Apr 11, 2026 560
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 3/2018 (ኢዜአ):- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የትንሳኤ በዓል የመልካም ምኞት መልዕክት ሙሉ ቃል ከዚህ እንደሚከተለው ቀርቧል:- እንኳን ለኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል አደረሳችሁ፣ አደረሰን! የትንሣኤ በዓል በክርስቲያኖች ዘንድ ልዩ ቦታ ያለው በዓል ነው። ሞት የተሻረበትና ሕይወት ዋስትና ያገኘበት ነው። ከሞት ባሻገር ሕይወት፣ ከመቃብር ባሻገር ትንሣኤ መኖሩ የታወጀበት ነው። ሞት መጨረሻ መቃብር መዳረሻ አለመሆናቸው የተረጋገጠበት ነው። በአዳም ምክንያት ወደ ምድር የወረደው ሰው፣ በክርስቶስ ምክንያት ወደላይ የወጣበት ነው። የዘንድሮውን ትንሣኤ የምናከብረው ሀገራችን ኢትዮጵያ በሚያልፍ ፈተና ውስጥ እንዳለች እያሰብን ነው። መንገዳችን ረጅም፣ ጉዟችን ፈታኝ መሆኑን እናውቃለን። ብርሃን እንዳናይ የሚጋርዱ፣ በጥልቁ ጨለማ ጠፍተን እንድንቀር አሥረው ለመያዝ የሚሞክሩ ወጥመዶች ብዙ ናቸው። ወደ ተስፋ ምድር እንዳንሻገር የሚጎትቱ ሰበቦች ሞልተዋል። ዳሩ ግን ከሕማማቱ ወዲያ ትንሣኤ፣ ከዕንቅፋቱ ባሻገር ስኬት እንደሚጠብቀን አምነን እንታገላለን። በትንሣኤው ዋዜማ - ርግጠኞች፣ ተስፈኞች፣ ተስፋ ቆራጮች፣ ወሬኞች፣ ተስፋ አስቆራጮች፣ ተጠራጣሪዎች ነበሩ። ርግጠኞቹ የሕማማቱ ፈተና እንደሚያልፍ ርግጠኞች ነበሩ። የዕለተ ስቅለት መከራ፣ለዕለተ ትንሣኤ ዋዜማ ለመሆኑ ርግጠኞች ነበሩ። የድንጋዩ በር፣ የበሩ ማኅተም እና የመቃብሩ ጠባቂዎች ትንሣኤውን እንደማያስቀሩት ርግጠኞች ነበሩ። የሚናፈሰው ወሬ እና የሚሠራጨው አሉባልታ እድሜው አጭር መሆኑን ርግጠኞች ነበሩ። ርግጠኞችም ስለሆኑ መሥዋዕትነትን ለመክፈል ዝግጁዎች ነበሩ። እውነቱን ለመመስከር ቆራጦች ነበሩ። በመስቀሉ ሥር ለመገኘት ደፋሮች ነበሩ። ተስፈኞቹ የርግጠኞቹን ያህል ሳያዩ የሚያምኑ አልነበሩም። ግን አንዳች መልካም ነገር ይጠብቁ ነበር። የተሰጠውን ትምህርት፣ የተደረገውን ተአምራት ሰምተዋል፤ አይተዋል፤ አንዳች ነገርም ጠብቀዋል። ነገር ግን ተገቢውን መሥዋዕትነት ለመክፈል ዝግጁዎች አልነበሩም። እውነትን ለመድፈር ቆራጦች አልነበሩም። ሐሰቱን ለመጋፈጥ ዐቅም አላገኙም። ቢያንስ ግን አንደበታቸውን ከክፉ ከልክለዋል። ተጠራጣሪዎች አጥር ላይ የነበሩ ናቸው። በጥብርያዶስ ይበላሉ፣ በጎልጎታ ይክዳሉ። በሆሳዕና ይዘምራሉ፣ በሊቶስጥራ ይሸሻሉ፡፡ ተአምር ለማየት ይመጣሉ፣መከራ ለማየት ይሳቀቃሉ፡፡ ከደስታው አውጡልኝ፣ ከመከራው ጦመኛ ነኝ የሚሉ ናቸው። ተስፋ ቆራጮች በሚያዩትና በሚሰሙት ቶሎ የሚወሰዱ ናቸው። በእውነትና በሐሰት፣ በፍርሃትና በጽናት መካከል ያለው ድንበር የጠፋባቸው ናቸው። ሕማማቱ ሲመጣ በቶሎ ወደ ትዝታ ገቡ። ሁሉንም ነገር የትናንት ታሪክ ብቻ አድርገው ወሰዱት። ሁሉንም ነገር “ልጡ የተራሰ፣ መቃብሩ የተማሰ” አድርገው ቆጠሩት። ከግራ ከቀኝ የሚሰሙት አሉባልታ፣ ከፊት ከኋላ የሚመጣው ጫጫታ፤ ከወዲህ ከወዲያ የሚማጣው እሳት፣ ከዚህም ከዚያም የሚያዩት መዓት አስፈራቸው። ነገን አስረሳቸው። በዚህ የተነሣ ተስፋ ቆርጠው ወደ ኋላ ተመለሱ። ወሬኞች ድሮም ወሬ ስቧቸው የመጡ ናቸው። ምን አለ፣ምን ተባለ ብለው የተሰባሰቡ ናቸው። የሰሙትንም ያልሰሙትንም፤ የሚያውቁትንም የማያውቁትንም፤ እውነቱንም ሐሰቱንም እያደባለቁ ኢየሩሳሌምን በወሬ ሞሏት። ቢያንስ ከትንሣኤው 15 ዓመት በኋላ ወንጌሉን የጻፈው ማቴዎስ፣ እስከዚያ ዘመን ድረስ ወሬው ብዙ ተቀባይ እንደነበረው ገልጧል። ተስፋ አስቆራጮች ዓላማቸው ሰውን ሁሉ ከትንሣኤ መንገድ ማራቅ ነበር። እነርሱም አይሄዱ፣ ሰውም አያስኬዱ። ከመጀመሪያው አልተቀበሉትም፤ በኋላም አልፈለጉትም። ብዙ ሰዎች እንደተከተሉት ሲያውቁ ደግሞ ቅናት አቃጠላቸው፤ ክፋት አንገበገባቸው። ክርስቶስን ከሰሱ፤ ራሳቸው ምስክር ሆኑ፤ በመጨረሻም ራሳቸው ፈረዱ። መቃብሩን ዘጉ፤ ጠባቂ አስቀመጡ። በማኅተም አሸጉ። ነገር፣ ያለቀና የተቆረጠ መሰላቸው። የትንሣኤ በዓል የእነዚህን ሁሉ እውነተኛ ማንነት የገለጠ ነው። ርግጠኞች የቆራጥነታቸው ውጤት በትንሣኤ አገኙ። ተስፈኞች እንዲህ ለሚያልፍ ጊዜ ባለመጽናታቸው አዘኑ። ተስፋ ቆራጮች አሻግሮ ማየት አቅቷቸው ከቦታቸው በመጥፋታቸው ተፀፀቱ። ወሬኞች በትንሣኤው እውነት የተነሣ ያ ሁሉ ወሬ እንደ ናቡከደነፆር ሐውልት ሲፈረካከስ አዩት። ተስፋ አስቆራጮች የገደሉት ክርስቶስ ሲነሣ፣ የዘጉት መቃብር ሲከፈት፣ ያተሙት ማኅተም ሲቀደድ፣ የመደቧቸው ጠባቂዎች ሲሸሹ በዓይናቸው በብረቱ አዩ። ትንሣኤው የሚነገር ሐቅ፣ የሚታይ እውነት ሆነ። ተጠራጣሪዎች ግን አሁንም አጥራቸው ላይ ሆነው ከግራም ከቀኝም ሳይሆኑ ቀሩ። የኢትዮጵያችንም ነገር እንዲሁ ነው። በኢትዮጵያ ለውጥ ርግጠኞች የሆኑት ዋጋ ይከፍላሉ፤ ርግጠኝነትን ፈርተው ተስፈኞች የሆኑት ቢያንስ አንደበታቸውን ከክፉ ይጠብቃሉ፡፡ ተስፋ ቆራጮች ነገን ማየት ስለሚሳናቸው መንገዳቸውን ይቀይራሉ፡፡ ወሬኞች አውርቶ አዳሪዎች በመሆናቸው የወሬ እንጀራ ይጋግራሉ። ተስፋ አስቆራጮች “ወተቱን አጥቁረው፣ ማሩን አምርረው” የዋሖችን አታለሏቸው፡፡ ተጠራጣሪዎች አንዴ ትኩስ አንዴ ቀዝቃዛ ሲሆኑ፣ ለብ ብለው ቀሩ። ኢትዮጵያችን ግን ትንሣኤዋን እያየች ነው። መግነዙን ፈትታዋለች፣ መቃብሩን ከፍታዋለች፤ ማኅተሙን ቀዳዋለች። ወሬኞች ከመቃብር ጠባቂዎች ጋር ተማክረው የሚያወሩትን ወሬ የምትሰማበት ጆሮ የላትም። ትንሣኤዋን አይለውጠውምና። እሷ ከዚህ በኋላ የምትጠብቀው ዕርገትን ነው። የምትጓዘው ኃይል እንደሚወርድላት አረጋግጣ ነው። ወደኋላ መመለስ የለም። ሕማማት አልፏል፤ዓርብም አልፏል፤ ቅዳሜም አልፏል። ትንሣኤ መጥቷል። በትንሣኤ ሌሊት የተኙ አልሰሙ ይሆናል። በተስፋ አስቆራጮች ተታለው የሄዱ ዜናው አልደረሳቸው ይሆናል። ትንሣኤ ግን እውን ሆኗል። ከቻላችሁ አጥር ላይ ያላችሁ ውረዱ። ተስፈኞች ርግጠኞች ሁኑ። ተጠራጣሪዎች እመኑ። ወሬኞች ከአፍ ወደ መዳፍ ተለወጡ። ምክንያቱም - ኢትዮጵያ ወደ ትንሣኤ ተቃርባለች። የኢትዮጵያ ትንሣኤ ከሚበሰርባቸው ምዕራፎች አንዱ ግንቦት ላይ የሚካሄደው ምርጫ ነው። ትንሣኤን ያለ ሕማማት እንደማናስበው ሁሉ ዴሞክራሲንም ከውጣ ውረድ ነጥሎ ማየት አይቻልም። በዓለም ላይ በደልዳላ መንገድ ተጉዞ ዴሞክራሲን የገነባ ሀገር የለም። ዴሞክራሲና ብልጽግና ያለ ጽናት አይሳኩም። ከእኛ በፊት ዐመጻውን በትዕግሥት የመከቱ ተሻግረዋል፤ ሑካታውን በጽናት ያለፉ አሳክተዋል። ብንመኝም ፈተናውን አናስቀርም፤ መጽናት ግን እንችላለን። ከድህነት መውጫው ብርታታችን፣ ወደ ዴሞክራሲ መድረሻችው ትዕግሥታችን እንደሆነ አምነን ለኢትዮጵያ ትንሣኤ በሙሉ ልባችን እንትጋ!! በድጋሚ መልካም የትንሣኤ በዓል ይሁንልን።ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!! ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ! ሚያዝያ 03 ቀን 2018 ዓ.ም
በዓሉን በአብሮነት እና በመተሳሰብ ለማሳለፍ ተዘጋጅተናል -የጅማ ከተማ የክርስትና እምነት ተከታዮች
Apr 11, 2026 113
ጅማ፤ ሚያዚያ 3/2018(ኢዜአ)፡- የትንሳኤ በዓልን በአብሮነት እና በመተሳሰብ ለማሳለፍ መዘጋጀታቸውን የጅማ ከተማ የክርስትና እምነት ተከታዮች ተናገሩ። የጅማ ከተማ ነዋሪው አንዱአለም አለማየሁ፣ በተለይም ባለፉት 7 ዓመታት አቅመ ደካሞችን በማገዝ፣ በመመገብ እና በመንከባከብ እያሳለፈ መሆኑን ይናገራል። "አልባሳትን ለሌላቸው በመስጠት፣ ከምንመገበው በማካፈል ለወገኖቻችን አለን ልንል ይገባል" የሚለው ወጣቱ፤ ሰዎች ካላቸው በማካፈል ለራሳቸው ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም ደስታ መትረፍ አለባቸው ሲል መልዕክቱን ያስተላልፋል። ሌላኛዋ ነዋሪ ሃና ፀጋዬ የፋሲካ በዓልን በየዓመቱ ወደ በጎ አድራጎት ተቋማት በመሄድ እንደምታሳልፍ ትናገራለች። "በዓሉ ሙሉ የሚሆነው የተቸገሩትን ስናስብ እና ከጎናቸው ስንቆም ነው" የምትለው ሃና፤ ዘንድሮም በከተማዋ ወደሚገኙት "የሰው ለሰው" እና "መቄዶንያ" በጎ አድራጎት ተቋማት በመሄድ በዓሉን ለማሳለፍ ዝግጅት ማድረጓን ተናግራለች። ሌላኛው ነዋሪ መኮንን ገብሩ በአካባቢያችን እና በጎረቤት ብዙ ሊታገዙ የሚገቡ ሰዎችን በማሰብ ከልጆቻቸው ጋር በደስታ እንዲያሳልፉ ልናግዝ ይገባል ብሏል። "በዓልን ያለ አብሮነት እና መተሳሰብ ማክበር ትርጉም አይሰጠኝም" የሚለው ደግሞ የጅማ ከተማ ነዋሪው ይሁኔ ጌታቸው ነው።   በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን የጅማ የም እና ሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ በበኩላቸው ''ክርስቶስ የተወልንን ምሳሌ በመከተል ለአቅመ ደካሞች ከማዘን ባለፈ በተግባር ከጎናቸው ቆመን ልናግዛቸው ይገባል'' ብለዋል። የትንሳኤ በዓል በዕምነቱ ተከታዩች ዘንድ ክርስቶስ ከሞት መነሳቱ የሚታሰብበት ትልቅ በዓል መሆኑን አስታውሰው ይህን በዓል ክርስቶስ የተወልንን ምሳሌ በመከተል አቅመ ደካሞችን በተግባር በማገዝ ማሳለፍ ያስፈልጋል ሲሉ ገልፀው እኛም ካለን በማካፈል ምሳሌዉን ልንከተል ይገባል ብለዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም