ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተናን በበይነ መረብ ለመፈተን የሚያስችል በቂ ልምምድ አድርገናል-በአዲስ አበባ ተፈታኝ ተማሪዎች
Jun 14, 2025 46
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተናን በበይነ መረብ ለመፈተን የሚያስችል በቂ ልምምድና ዝግጅት ማድረጋቸውን በአዲስ አበባ የዘንድሮ ተፈታኝ ተማሪዎች ተናገሩ፡፡ በአዲስ አበባ ለተፈታኝ ተማሪዎች በበይነ መረብ ለሚሰጠው ፈተና የመጨረሻ የልምምድ ፈተና ዛሬ ተሰጥቷል፡፡ የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ከሰኔ 23 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሀምሌ 8 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ እንደሚሰጥ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት ይፋ ማድረጉ ይታወሳል። በዚሁ ወቅት ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ ትምህርት ቤቶች የ12ኛ ክፍል ተፈታኝ ተማሪዎች እንደተናገሩት በበይነ መረብ ለሚሰጠው ፈተና በቂ ልምምድ ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡ ፈተናው በበይነመረብ መሰጠቱ በቀጣይ ብቁና ተወዳዳሪ ለመሆን ቴክኖሎጂን ይበልጥ እንዲለማመዱ እድል የሚሰጥ መሆኑን አስታውቀዋል ፡፡ አስተያየታቸውን ከሰጡ የ12ኛ ክፍል ተፈታኝ ተማሪዎች መካከል ተማሪ ዮርዳኖስ ፍቃዱ እንዳለችው ፈተናው በበይነ መረብ መሰጠቱ ብቁና ተወዳዳሪ ለመሆን የቴክኖሎጂ እውቀትን ለማዳበር ትኩረት እንድንሰጥ ያስችለናል ብላለች። ፈተናውን በራሳችን ዝግጅት ላይ ተመስርቶ በመስራት የጥረታቸንን ዋጋ እንድናገኝ በማድረግ በኩል ትልቅ ጠቀሜታ አለው ያለችው ደግሞ ተማሪ ሜሮን እንዳለ ነች። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ተማሪ ናታኒም ኤሊያስ እንዳለችው፤ በዛሬው እለት የወሰዱት የመጨረሻ የልምምድ ፈተና ለዋናው ፈተና ብቁ እንዲሆኑ ሚያስችላቸው መሆኑን ነው የገለጸችው፡፡ ተማሪዎቹ በበይነ መረብ ለሚሰጠው ፈተና በቂ ዝግጅት ለማድረግ በዛሬው እለት የመጨረሻ የልምምድ ፈተና በመፈተን ጥሩ ዝግጅት ማድረጋቸውንም ተናግራለች። በልምምድ ወቅት መምህራኖቻቸው የተለያዩ ጥያቄዎችን በማዘጋጀት ለፈተናው እንዲዘጋጁ የሚጠበቅባቸውን ሲያደርጉ እንደነበር የገለጸው ደግሞ ተማሪ ዳግማዊ ታደሰ ነው፡፡ በዛሬው እለት ያደረጉት የመጨረሻ የልምምድ ፈተናም ክፍተቶቻቸውን ለይተው በማስተካከል ለዋናው ሀገር አቀፍ ፈተና እንዲዘጋጁ ያሚያደርጋቸው መሆኑን ተናግሯል፡፡ የመጨረሻው ልምምድ ለዋናው ፈተና ያደረኩትን ዝግጅት ለመፈተሽ ያስቻለኝ ነው ስትል የገለጸችው ደግሞ ተማሪ ዮርዳኖስ አበበ ነች፡፡ ከዚህ ቀደም ተደጋጋሚ ልምምዶችን እና በቂ ዝግጅት በማድረግ ሀገር አቀፍ ፈተናውን በመጠባበቅ ላይ መሆኑን የገለጸው ደግሞ ተማሪ አቤኔዘር ፍቃዱ ነው፡፡
ዜጎች ደምና የዓይን ብሌን በመለገስ የሚያበረክቱትን በጎ ተግባር አጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል
Jun 14, 2025 48
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ዜጎች ደምና የዓይን ብሌን በመለገስ የሚያበረክቱትን በጎ ተግባር አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ ገለጹ። ዓለም አቀፍ የደም እና የዓይን ብሌን ለጋሾች ቀን በአዲስ አበባ የዓድዋ ድል መታሰቢያ በተለያዩ መርሀ ግብሮች እየተከበረ ይገኛል። የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ በመርሀ ግብሩ ላይ እንደገለፁት፤ በኢትዮጵያ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እየዳበረ ሲሆን በህብረተሰቡ ዘንድም ደም መለገስ እየተለመደ ነው። ይሁን እንጂ ደም የመለገስ ተግባር ወጥነት እንደሌለው ያነሱት ዶክተር መቅደስ፤ በዘመቻና በንቅናቄ ተግባራት ላይ መመስረቱ ውስንነት እንዲያጋጥመው አድርጎታል ብለዋል። ህብረተሰቡ በራሱ ተነሳሽነት ደም የመለገስ ተግባርን ቀጣይነት ባለው መልኩ እንዲያከናውንም ጥሪ አቅርበዋል። ይህም በደም መፍሰስ ምክንያት የሚከሰት የእናቶች ሞት ለማስቀረት የሚደረገውን ጥረት ከዳር ለማድረስ አይነተኛ ሚና እንዳለው አመልክተዋል። በተለያየ የጤና እክል ምክንያት በቋሚነት ደም ለሚያስፈልጋቸው፣ በተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ አደጋ የደም እጥረት ለሚያጋጥማቸው ሰዎችም የደም አቅርቦት ወሳኝ በመሆኑ ደም የመለገስ ልምዱ እየተጠናከረ መሄድ እንዳለበት ጠቁመዋል። መንግስት የደም ባንኮችን፣ የህክምና ተቋማትንና መሰል ግብዓቶችን በማሟላት ረገድ እያከናወነ ባለው ተግባር አበረታች ውጤት መመዝገቡንም ገልጸዋል። የጤና አገልግሎትን ወጥና ተደራሽ ለማድረግ ዜጎች ደምና የዓይን ብሌን በመለገስ የሚያበረክቱትን አስተዋፅኦ አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ነው ዶክተር መቅደስ የገለጹት። የኢትዮጵያ ደምና ሕብረ ህዋስ ባንክ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አሸናፊ ታዘበው በበኩላቸው፤ አንድ ሰው ደምና የዓይን ብሌን በሚለግስበት ወቅት ተስፋን፣ የወደፊት ብርሀንና ህይወትን መስጠት መሆኑን አስታውቀዋል። ይህም ከስጦታዎች ሁሉ የላቀ ስጦታ መሆኑን ነው የገለጹት። በመረሀ ግብሩ ላይ በተከታታይ ደም የለገሱ ሰዎች እውቅና የተ ሰጣቸው ሲሆን፤ ሰዎች ከህልፈት በኋላ የዓይን ብሌንን እንዲለግሱ ጥሪ የሚቀርብበት ነውም ብለዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ በሰኔ ወር እየተከበረ ያለው 21ኛው የደምና የዓይን ብሌን ለጋሾች ቀን "የሕይወትና የብርሀን ስጦታ! ደም ይለግሱ፤ ብሌንዎን ቃል ይግቡ" በሚል መሪ ሀሳብ ነው እየተከበረ ያለው።
የትራፊክ አደጋን በተቀናጀ መንገድ ለመከላከል የተጀመሩ ስራዎች ይጠናከራሉ - አገልግሎቱ
Jun 14, 2025 45
ድሬደዋ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፡- የትራፊክ አደጋን በተቀናጀ መንገድ ለመከላከል የተጀመሩ አበረታች ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የፌደራል የመንገድ ደህንነት እና መድን ፈንድ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈፃሚ ጀማል አባሦ ተናገሩ። የፌዴራልና የክልሎች የዘርፉ አመራሮች በምስራቅ የኢትዮጵያ ክፍሎች የትራፊክ አደጋን ለመከላከል እየተከናወኑ የሚገኙ ተግባራትን በመመልከት የዘርፉን አፈጻጸም በድሬዳዋ እየገመገሙ ነው። በመርሃ ግብሩ የተሳተፉት የአገልግሎቱ ዋና ስራ አስፈፃሚ ጀማል አባሦ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ የትራፊክ አደጋ በሰውና በሀገር ንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ነው። ችግሩን በተቀናጀ መንገድ ለመከላከል የ10 ዓመታት የተናበበ ስትራቴጂክ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ስራ መገባቱን ጠቅሰው፤ ባለፉት አምስት ዓመታት በተከናወኑ የተቀናጁ ስራዎች ለውጥ ማምጣት መቻሉን አውስተዋል። ይህንን ለውጥ በከፍተኛ ደረጃ ለማሳደግ አዳዲስ ዲጂታል ሪፎርሞች፣ ዘመናዊ አሰራሮችና ህጎች በመተግበር ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። በተለይ በምስራቅ ተጎራባች ክልሎች እየተገነቡ የሚገኙት የኮሪደር ልማቶች የትራፊክ ፍሰትን አስተማማኝ በማድረግ አደጋን ለማስቀረት ወሳኝ አስተዋጽኦ እንደሚኖራቸው አንሰተዋል። እንደ ሀገር የተጀመረውን ዲጂታል የትራፊክ አደጋ የመከላከል ስራ በትክክል ዕውን በተደረገበት ድሬዳዋ መሠረታዊ ለውጥ ማምጣቱን ጠቅሰው ተሞክሮውን በማስፋት አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል ሲሉም ገልጸዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ባለስልጣን ዋና ስራ አስፈፃሚ ወይዘሮ ሹክሪ አብዱረህማን በበኩላቸው፤ ባለስልጣኑ ከፍትህ እና ከትራፊክ ተቋማት ጋር ቅንጅት በመፍጠር አበረታች ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። በተለይ ከትምህርት ቤቶችና ሌሎች ባለድርሻዎች ጋር የተቀናጀ የትራፊክ አደጋ የመከላከል ስራ በመሰራቱ አደጋው እየቀነሰ መምጣቱን ተናግረዋል። በምስራቅ ተጎራባች ክልሎች የተካሄደው የስራ ጉብኝት ለቀጣይ ስራ ጥሩ መደላድል እንደሚፈጥር በመግለጽ።
ማህበሩ ለእናቶች ማቆያ አገልግሎት የሚውል የቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ
Jun 14, 2025 129
ባህርዳር፤ ሰኔ 7/2017 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ሚድዋይፎች ማህበር በአማራ ክልል በደቡብ ጎንደርና ሰሜን ጎጃም ዞኖች ለሚገኙ ሁለት ጤና ጣቢያዎች ለእናቶች ማቆያ አገልግሎት የሚውል የቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ። የማህበሩ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ፈቃዱ ማዘንጊያ በድጋፍ ርክክቡ ወቅት እንደገለጹት ማህበሩ ግምታቸው 2 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ የቁሳቁስ ድጋፉን ያስረከበው ለክልሉ ጤና ቢሮ ነው። ድጋፉም በደቡብ ጎንደር ጋህሳይና በሰሜን ጎጃም ሳንክራ ጤና ጣቢያዎች ለተገነቡ የእናቶች ማቆያ ማዕከላት መሆኑንም ስራ አስኪያጁ ገልፀዋል። ድጋፍ ከተደረጉት ቁሳቁስም አልጋዎች፣ የልብስ ማጠቢያ ማሽኖች፣ የማብሰያ፣ የመመገቢያ ወንበሮችና ጠረጴዛዎች፣ ቴሌቪዥን፣ ብርድ ልብስ፣ ለምግብ አገልግሎት የሚውል ዱቄትና ሌሎችም ይገኙበታል። ቀደም ሲልም ማህበሩ የእናቶችና ህፃናት ሞትን ለመቀነስ በክልሉ በዋግህምራ፣ ሰሜንና ደቡብ ወሎ እንዲሁም ሰሜን ሸዋ ዞኖች ለሚገኙ አምስት ጤና ተቋማት ተመሳሳይ ድጋፍ ማድረጉን ተናግረዋል። እንዲሁም በአገር አቀፍ ደረጃ በአፋር፣ በትግራይ፣ በኦሮሚያና በሲዳማ ክልሎች ማህበሩ መሰል ድጋፎችን በማድረግ የእናቶችና ህፃናት ሞትን ለመቀነስ ሙያዊ ግዴታውን እየተወጣ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። የክልሉ ጤና ቢሮ ተወካይ ዶክተር ቤተልሄም መኮንን እንዳሉት ማህበሩ በሁለት ጤና ጣቢያዎች ለተገነቡ የእናቶች ማቆያ ማዕከላት ያደረገው ድጋፍ የነበረውን የቁሳቁስ ችግር ሙሉ በሙሉ የቀረፈ ነው ብለዋል። ይህም ራቅ ካሉ አካባቢዎች የሚመጡ ነፍሰ-ጡር እናቶች በማቆያ ማዕከላቱ ሳይቸገሩ ተገቢውን አገልግሎትና የባለሙያ ክትትልና ድጋፍ አግኝተው እንዲወልዱ የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። ማህበሩ የእናቶችና ህፃናት ሞትን ለመቀነስ እየተደረገ ያለውን ጥረት ለማገዝ እያደረገ ያለው የቁሳቁስ ድጋፍ ለታለመለት ዓላማ እንዲውል ቢሮው አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ያደርጋል ብለዋል። ''ለጋህሳይ ጤና ጣቢያ የእናቶች ማቆያ የተደረገው የቁሳቁስ ድጋፍ የነበረውን ችግር ሙሉ በሙሉ የቀረፈ ነው'' ያሉት ደግሞ የደቡብ ጎንደር ዞን ጤና መምሪያ ተወካይ ኃላፊ አቶ ኃይለኢየሱስ ዳኘው ናቸው። በክልሉ ከተገነቡ 727 የእናቶች ማቆያ ማዕከላት 544ቱ በአሁኑ ወቅት የተሟላ አገልግሎት ለነፍሰ-ጡር እናቶች እየሰጡ እንደሚገኙም ከክልሉ ጤና ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በምስራቅ ቦረና ዞን ከ115 ሺህ ለሚበልጡ የቀንድ ከብቶች፣ በጎችና ፍየሎች የበሽታ መከላከያ ክትባት ተሰጠ
Jun 14, 2025 51
ነገሌ ቦረና፣ ሰኔ 7/2017 (ኢዜአ) - በምስራቅ ቦረና ዞን ከ115 ሺህ ለሚበልጡ የቀንድ ከብቶች፣ በጎችና ፍየሎች የበሽታ መከላከያ ክትባት መሰጠቱን የዞኑ አርብቶ አደር ልማት ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የእንስሳት ጤና ባለሙያ አቶ ቦነያ አሬሮ ለኢዜአ እንደገለጹት እንስሳቱን ከሳንባ ምች፣ ከአባ ሰንጋ፣ ከአባ ጎርባ፣ ከቆዳና ከሌሎችም በሽታዎች ለመከላከል የሚያስችል ክትባት ተሰጥቷል። ክትባቱ ቆላማ በሆኑ ሊበን፣ ጎሮዶላ፣ አሬሮ፣ ዋጭሌ፣ ዳስና ጉሚ ኤልዳሎ ወረዳዎች እንደውም ወይናደጋማ በሆኑ መዳ ወላቡና ወላቡ ሊጣ ወረዳዎች መሰጠቱን ጠቅሰዋል። በወረዳዎቹ 400 ሺህ ለሚሆኑ የቀንድ ከብቶች፣ በጎችና ፍየሎች ለመስጠት ታቅዶ እሰካሁን ለ115 ሺህ 480ዎቹ መሰጠቱን ተናግረዋል። በታቀደው መሰረት ክትባቱን ለማዳረስ በ600 የእንስሳት ጤና ባለሙያዎችና ድጋፍ ሰጭ ሰራተኞች በመታገዝ እየተሰጠ መሆኑን አስታውቀዋል ።
በክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት 2 ሺህ 500 ቤቶችን በ90 ቀናት መልሶ ለመገንባት አቅደናል--ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jun 14, 2025 51
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ በዘንድሮው የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት በከፍተኛ ትኩረት 2 ሺህ 500 ቤቶችን በ90 ቀናት መልሶ ለመገንባት መታቀዱን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለፁ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2017 የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት መክፈቻ መርኃ-ግብር ተካሂዷል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 የቤት ማደስ ስራን አስጀምረዋል። ከንቲባ አዳነች በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ባህል ሆኖ መቀጠል ያለበት መልካም ተግባር ነው። በዚህም የበጎ ፍቃደኝነት አገልግሎት የአንድ ወቅት የንቅናቄ ስራ ብቻ ሳይሆን የሁልጊዜ ተግባር እና ባህል ማድረግ እንደሚገባ ተናግረዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በከተማዋ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችንና ባለሃብቶችን በማስተባበር የበጎ ሥራ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል። በ2017 የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት 18 ሰው ተኮር የሆኑ የተለያዩ የበጎ ፍቃድ አገልግሎቶችን ለመተግበር መታቀዱን አብራርተዋል። በመርኃ ግብሩ ከተማዋን ምቹ እና ለኑሮ ተስማሚ እንድትሆን የሚያስችሉ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ሥራዎች እንደሚከናወኑ ከንቲባዋ አስታውቀዋል ። በተጨማሪም ለአቅመ ደካማ ነዋሪዎች በድግግሞሽ ማዕድ የማጋራት ፣ወላጅ የሌላቸዉ ህፃናት አሳዳጊና ተንከባካቢ ቤተሰቦች የሚያገኙበት፣በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል ከተማችንን አረንጓዴ የምናለብስበት ነው ብለዋል። ከሁሉ በላይ በክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት በከፍተኛ ትኩረት 2 ሺህ 500 ቤቶችን በ90 ቀናት መልሶ ለመገንባት መታቀዱንም ነው የገለጹት። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፍቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽነር ይመር ከበደ የክረምት ወቅት ለበጎ ፍቃድ ስራ ምቹ እና ተስማሚ ወቅት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ለዚህም ከተማ አስተዳደሩ ልዩ ትኩረት በመስጠት እየሰራበት እንደሚገኝ ጠቁመው ለስራው የሚያግዙ ቋሚ በጎ ፍቃደኞችን በማሰልጠን ከዛሬ ጀምሮ ወደ ስራ ማስገባቱን አስታውቀዋል።
ህገ-ወጥ የምግብና የመድሃኒት ዝውውርን ለመከላከል የባለድርሻ አካላት ቅንጅት መጠናከር አለበት - ባለስልጣኑ
Jun 14, 2025 40
ሀዋሳ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ ህገ-ወጥ የምግብና መድሃኒት ዝውውርን ለመከላከል የባለድርሻ አካላት ቅንጅት መጠናከር እንዳለበት የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን አስታወቀ። ባለስልጣኑ ከምግብና የጤና ግብዓቶች ቁጥጥር ባለድርሻ አካላት ጋር በሀዋሳ ከተማ ምክክር አድርጓል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሄራን ገርባ በወቅቱ እንደገለጹት ባለስልጣኑ ባለፉት ሁለት ዓመታት የምግብና መድኃኒት ቁጥጥሩን የሚያጠናክሩ የሪፎርም ስራዎችን በመተግበር ዘርፈ ብዙ ተግባራትን አከናውኗል። በዚህም የተመዘገቡ በርካታ ውጤቶች ቢኖሩም ያልተፈቱ ችግሮች በመኖራቸው ህገ-ወጥ የምግብና መድኃኒት ዝውውርን ለመከላከል የባለድርሻ አካላት ቅንጅት መጠናከር አለበት ብለዋል። ህገ-ወጥ የምግብና የመድኃኒት ዝውውር በሀገሪቱ እየጨመረ ለመጣው ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች መስፋፋት ምክንያት ሊሆን እንደሚችልም ገልጸዋል። ዳይሬክተሯ አክለውም በምግብ ላይ ባዕድ ነገር መደባለቅ፣ ጥራትና ደህንነታቸው ያልተረጋገጡ መድኃኒቶችን በህገወጥ መንገድ በመሸጥ ህብረተሰቡ ላይ ጉዳት የሚያደርሱ አካላትን ለህግ የማቅረብ ስራ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ባለፉት 11 ወራት 243 የምግብ፣ የመድኃኒትና የህክምና መሳሪያዎች አስመጪና አከፋፋዮች መታገዳቸውንና የ129ኙ ፈቃድ መሰረዙን ገልጸዋል። በተጨማሪም ለበርካታ ተቋማት የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ መሰጠቱንና የታሸጉ መኖራቸውንም ጠቅሰዋል። የሲዳማ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ሰላማዊት መንገሻ በበኩላቸው በባለስልጣኑ የሚከናወኑ ተግባራት የማህበረሰቡን ጤንነትና ደህንነት ለማስጠበቅ ጉልህ ድርሻ ያላቸው ናቸው። በክልሉ በዕቅድና በድንገተኛ ፍተሻ በህገወጥ የምግብና የመድኃኒት ዝውውር መከላከል ላይ በቅንጅት የተሰሩ ስራዎች ተስፋ ሰጪ ውጤቶች የተመዘገቡባቸውና መጠናከር ያለባቸው ናቸው ብለዋል። በመሆኑም ባለድርሻ አካላት በመድረኩ የሚገኙ ግብዓቶችን የቀጣይ ዕቅድ አካል በማድረግ በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን በመቅረፍ የህዝቡን ጤና ማስጠበቅ ላይ በትኩረት መስራት እንዳለባቸውም ገልጸዋል። በክልሉ ህብተሰቡን ባለቤት ያደረገ የቁጥጥር ስራ እየተከናወነ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ጤናና ጤና ነክ ግብዓት ጥራት ቁጥጥር አገልግሎት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ቡሪሶ ቡላሻ ናቸው። በዚህም ባለፈው አንድ ዓመት ምግብን ከባዕድ ነገር ጋር በመቀላቀልና ህገ-ወጥ የመድኃኒት ዝውውር ላይ ተሳትፈው በተገኙ 16 ግለሰቦች ላይ ህጋዊ እርምጃ ተወስዷል ብለዋል። በቀጣይም የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት በማጠናከር ጉዳዩ በጤና ላይ እያስከተለ ያለውን ዘርፈ ብዙ ችግር ለመቅረፍ በትኩረት ይሰራል ነው ያሉት። በመድረኩ በባለስልጣኑና በሲዳማ ክልል ያለፉት ወራት አፈጻጸሞች ላይ ያተኮረ ውይይት ተደርጓል።
ኢትዮጵያ ስደተኞችን በተመለከተ የምትከተለው አካታች መርሃ ግብር በአርአያነት የሚወሰድ ነው - የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ
Jun 14, 2025 54
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ስደተኞችን በተመለከተ የምትከተለው አካታች መርሃ ግብር በአርአያነት ሊወሰድ የሚችል መሆኑን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ ተናገሩ። የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ስደተኞችን በአካታችነት መደገፍን የተመለከተ ከፍተኛ የውይይት መድረክ በአዲስ አበባ አካሂዷል። የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት ኢትዮጵያ በስደተኞች ዙሪያ እየተገበረችው ያለው ፖሊሰ የሚደነቅ ነው። በተለያዩ ክልሎች የሚገኙ የስደተኛ መጠለያ ጣቢያዎችን በጎበኙበት ወቅት የተሻለ አገልግሎት እየተሰጣቸው መሆኑን ማረጋገጥ ችያለሁ ብለዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ስደተኞችን ታሳቢ ያደረገ አካታች መርሃ ግብር ተግባራዊ በማድረግ በትምህርት፣ በጤና፣ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ በዲጂታል አካታችነትና ሌሎች አገልግሎቶች ተጠቃሚ አድርጓል ነው ያሉት። በመሆኑም ኢትዮጵያ ስደተኞችን በተመለከተ የምትከተለው አካታች መርሃ ግብር ሌሎች ሀገሮችም በአርአያነት በመውሰድ ሊያሰፉት የሚገባ መሆኑን ነው ያስገነዘቡት። ስደተኞች በአካታች መርሃ ግብሮች በምጣኔ ሃብት ውስጥ ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማድረግ በዘላቂነት እራሳቸውን እንዲችሉ ማድረግ ሰብዓዊ ድጋፍን መቀነስ በመሆኑ የሚበረታታ እንደሆነ ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ በሯን ክፍት አድርጋ ስደተኞችን በመቀበል በአካታችነት ለማስተናገድ እያከናወነችው ያለውን ተግባር አለም አቀፍ ማህበረሰብ ሊደግፍ እንደሚገባ በአጽንኦት አንስተዋል። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ የረጅም ጊዜ ታሪክ አላት። ስደተኞችን በአካታችነት በመቀበል የጤና፣ የትምህርትና ሌሎች አገልግሎቶችን በመስጠትና በምጣኔ ሃብት በዘላቂነት ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ በፖሊሲ ደረጃ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች እንደምትገኝ አስረድተዋል። በተመሳሳይ መሰረታዊ በሆኑ አገልግሎቶች በወሳኝ ኩነት እንዲሁም ዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። በትምህርት ዘርፍ በመጀመሪያ ደረጃ፣ በቴክኒክና ሙያ እንዲሁም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የትምህርት አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ ችላለች ብለዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታዋ ገለጻ፤ በምጣኔ ሃብት ዘርፍም በስራ ዕድል ፈጠራ በማካተት በዘላቂነት ራሳቸውን የሚችሉበት ዕድል የተፈጠረ ሲሆን፤ አብዛኞቹ ስደተኞች ይህን ዕድል እየተጠቀሙበት መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ስደተኞችን ታሳቢ ያደረገ የተቀናጀ እና አካታች አሰራሩን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ጠይባ ሃሰን እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ስደተኞችን ተቀብላ እያስተናገደች ትገኛለች። ስደተኞችን በአካታችነት በመደገፍ በቀጣይ የትምህርት፣ የጤና፣ የኢንተርኔት ተደራሽነትና ሌሎች አገልግሎቶችን የበለጠ ለማጠናከርም ይሰራል ብለዋል። መንግስት በዘላቂነት ስደተኞች ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ እየተገበራቸው ላሉ የተለያዩ መርሃ ግብሮች ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የቴክኒክና የገንዘብ ትብብሩን ሊያጠናክር ይገባል ብለዋል። በኢትዮጵያ የተ.መ.ድ ዋና ተጠሪና የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ራሚዝ አልካባሮቭ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ለስደተኞች ሁልጊዜም በሯን ክፍት በማድረግ የምትቀበል ሀገር ናት ብለዋል። በመሆኑም የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በጀቱን በማሳደግ መንግስት እያከናወነ ያለውን ተግባር ሊደግፍ ይገባል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ ተግባራዊ እያደረገችው የሚገኘውን አካታች መርሃ ግብር እንደሚደግፉ በመድረኩ የተገኙ የተለየዩ ሀገራት አምባሳደሮች፣ አለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮች፣ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች አረጋግጠዋል።
በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት 2ሺህ 500 ቤቶችን ለመገንባት እቅድ ተይዟል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jun 14, 2025 61
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ በ2017 ዓ.ም የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት 2 ሺህ500 ቤቶችን ለመገንባት እቅድ መያዙን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ አስታወቁ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2017 የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት መክፈቻ መርኃ-ግብር ተካሂዷል። በመርኃ ግብሩ ማስጀመሪያ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽነር ይመር ከበደ እና የአስተዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ከንቲባ አዳነች በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ባህል ሆኖ መቀጠል ያለበት መልካም ተግባር ነው። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በከተማዋ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችንና ባለሃብቶችን በማስተባበር የበጎ ሥራ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል። በ2017 የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በርካታ ሰው ተኮር ተግባራት እንደሚፈጸሙ ገልጸው፤ 18 የተለያዩ በጎ ፈቃድ ተግባሮችን ለመተግበር መታቀዱን አብራርተዋል። ከተማዋን ምቹ እና ለኑሮ ተስማሚ እንድትሆን የሚያስችሉ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራዎች እንደሚከናወኑ ከንቲባዋ ገልፀዋል። በዚህ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት መርኃ ግብር 2 ሺህ 500 ቤቶችን በ90 ቀናት ለመገንባት መታቀዱንም ነው የገለጹት። በተጨማሪም 500 ሺህ ለሚሆኑ ለከተማዋ ነዋሪዎች በድግግሞሽ ማዕድ የማጋራት ዕቅድ መያዙንም አመልክተዋል።
መምህራን እውነትና እውቀትን መለኪያ በማድረግ በትውልድ እና በሀገር ግንባታ ላይ የመሪነት ሚናቸውን ሊያጠናክሩ ይገባል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jun 13, 2025 83
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ መምህራን እውነትና እውቀትን መለኪያ በማድረግ በትውልድ እና በሀገር ግንባታ ላይ የመሪነት ሚናቸውን ሊያጠናክሩ እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አስገነዘቡ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከመላው ኢትዮጵያ ከተውጣጡ መምህራን ጋር ውይይት አካሂደዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከመምህራን ለተነሱ ጥያቄዎች በሰጡት ማብራሪያ፤ መምህራን በእውቀትና እውነት ላይ የተመሰረቱ በመሆናቸው ሀሳባቸው ለፖሊሲ ግብዓትነት እንደሚውል ተናግረዋል፡፡ የአያት እና ቅድመ አያቶቻችን ዘመን የተለያዩ እንደነበሩ ጠቅሰው፤ የእኛ ዘመን ደግሞ የተለየ ዓለም መሆኑን መረዳት ይገባል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ እውቀትና እውነት መለኪያ እንዲሆኑ መምህራን ተግተው መስራት አለባቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሁን ያለውን ለማሳነስ የሌለ ድሮ ማንሳት እንደማይገባ ገልጸዋል፡፡ እውነትና እውቀት ፈታኝና ዋጋ የሚያስከፍሉ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ብዙዎች የጥፋት አካሄድ የሆነውን ቀላሉንና አቋራጭ መንገድ ይከተላሉ ብለዋል፡፡ አሁን ያለንበት የድህረ እውነት ዘመን ውሸትና ጩኸት የነገሰበት ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አለመስራት ብቻ ሳይሆን የተሰራ እንደሚያፈርስ ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም መምህራን ከባዱንና ፈታኝ የሆነውን እውነትና እውቀት በመፈለግ ትውልድ ማሻገርና ሀገር መገንባት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል፡፡ የመምህራን ተሰጥኦ መድከም፣ መስራትና ሀገር ማሻገር በመሆኑ ከእለት ጉርስ አልፎ ማሰብ የሚችል ትውልድ ሊፈጥሩ እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ለልጆቻችን የተሻለች ሀገር ለማውረስ ድህነት በቃን፣ ልመና ሰለቸን ብለን ጥሪታችንን አሟጠን ልማት ላይ ማዋል ይገባናል ብለዋል፡፡ በዚህ ስሜት በገነነበት፣ እውነት በኮሰመነበት ዘመን መምህራን እውነትና እውቀት የሚገዳቸው እንጂ ዘረኝነት የሚያስጨንቃቸው ሊሆኑ አይገባም ነው ያሉት፡፡ መምህራን የትናንትን ታሪክ እና የዛሬውን ነባራዊ ሁኔታ ብቻ ሳይሆን የመጪውን ዘመን ደረጃ ጭምር መገንዘብ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡
መምህራን በድህረ እውነት ዘመን እውቀት እና እውነት እንዲነግሱ የማድረግ ኃላፊነት አለባቸው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jun 13, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ መምህራን በድህረ እውነት ዘመን እውቀት እና እውነት ነግሰው እንዲወጡ የማድረግ ወሳኝ ኃላፊነት እንዳለባቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከመላው ኢትዮጵያ ከተውጣጡ መምህራን ጋር ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አሁን ያለንበት ዘመን ውሸት እና ጩኸት የነገሰበት ነው፤ ውሸት እና ጩኸት ደግሞ የተሰራ ነገር ያፈርሳል ብለዋል። የድህረ እውነት ዘመን መዳረሻ አላማ እና ግብ የሌለው ከዕለት ጉርስ ያለፈ ነገር ማየት የማይችል ትውልድ መፍጠር መሆኑን አመልክተዋል። ይህም ከምክንያታዊነት እና እውነታ ይልቅ ስሜታዊነት ይበልጥ እንዲጎላ የሚያደርግ እንደሆነም ነው የተናገሩት። መምህራን በዚህ የድህረ እውነት ዘመን እውነት እና እውቀት አሸንፈው እንዲወጡ የበኩላቸውን ኃላፊነት እንዲወጡም አስገንዝበዋል። መምህራን የትናንት ታሪክን በማወቅ፣ ዛሬ በመረዳትና ነገን በመገንዘብ የተሻለች ኢትዮጵያን ለቀጣዩ ትውልድ በማስረከብ በኩልም ጉልህ ድርሻ እንዳላቸው ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከችግር፣ ከድህነት፣ ከመከፋፈል እና ከልመና ለማውጣት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ሚናቸው ወሳኝ መሆኑን ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት።
የጋራ ትርክት ግንባታ ላይ መምህራን የበኩላቸውን ሚና መወጣት አለባቸው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jun 13, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ የጋራ ትርክት ግንባታ ላይ መምህራን የበኩላቸውን ሚና መወጣት እንዳለባቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከመላው ኢትዮጵያ ከተውጣጡ መምህራን ጋር ውይይት አካሂደዋል። በውይይታቸው ከመምህራኑ ለተነሱ በርካታ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ መንግስት የጋራ ትርክት ለመገንባት ስትራተጂ እና ዕቅድ አዘጋጅቶ እየሰራ መሆኑን ገልጸው፤ መምህራን ይህን መልካም ስራ በአግባቡ ተገንዝበው መደገፍ እንዳለባቸው አስረድተዋል። የጋራ ትርክትን ስኬታማ ለማድረግ በትምህርት ቤቶች ሁልጊዜ ማስገንዘብ እንደሚገባ ገልጸው፤ ለዚህም መምህራን የድርሻቸውን መወጣት አለባቸው ብለዋል። መንግስት ያደሩ ችግሮችን በአምስት ማዕቀፎች ለመፍታት መወሰኑን አንስተው ችግሮችን በውይይትና በመደማመጥ እንፍታ በሚል በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በማቋቋም ወደ ተግባር መግባቱ አንዱና ዋነኛው መሆኑን ተናግረዋል። ሁለተኛው ደግሞ የሽግግር ፍትህ በማቋቋም ያደሩ ችግሮችን በዘላቂነት በይቅርታና በፍትህ ለመፍታት የጀመረው ሥራ ስለመሆኑም አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሶስተኛውን ማዕቀፍ ሲያስረዱ ብሔራዊ የተሃድሶ ኮሚሽን በማቋቋም የቀድሞ ታጣቂዎች ተሃድሶ ወስደው በሰላማዊ መንገድ ህይወታቸውን እንዲመሩ በማድረግ ረገድ ትልቅ ስራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ስብራት ለማስተካከል ሀገር በቀል የብዝሃ ዘርፍ የኢኮኖሚ ማሻሻያ በማድረግ ስኬቶችን ማስመዝገቡን ደግሞ በአራተኛ ማዕቀፍ ጠቅሰዋል። ጠንካራ ተቋማት የመገንባትና የመንግት አገልግሎትን የማዘመን ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑንም በአፅንኦት ገልጸዋል።
በሱዳን በተከሰተው ግጭት ምክንያት ወደ ሀገራቸው የተመለሱ ዜጎችን መልሶ ለማቋቋም በቅንጅት መስራት ይገባል
Jun 13, 2025 77
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ በሱዳን በተከሰተው ግጭት ምክንያት ወደ ሀገራቸው የተመለሱ ዜጎችን በዘላቂነት መልሶ ለማቋቋም በቅንጅት መስራት እንደሚገባ ተገለጸ፡፡ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር እና ፍትህ ሚኒስቴር ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በሱዳን በተከሰተው ግጭት ተፈናቅለው ወደ ሀገራቸው የተመለሱ ዜጎችን መልሶ ማቋቋም ላይ ትኩረት ያደረገ ምክክር እያካሄዱ ነው። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ሃላፊ አሳልፈው አህመዲን እንደገለጹት፤ ሚኒስቴሩ መደበኛ ያልሆነ ፍልሰትን ከመከላከል ጎን ለጎን ተመላሽ ዜጎች ማህበራዊ፣ ስነ ልቦናዊ እና ኢኮኖሚያዊ ድጋፍ እንዲያገኙ እየሰራ ይገኛል፡፡ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በተለይ ህጻናት፣ ሴቶችና አረጋውያን ሰብዓዊ ጉዳት እንዳይደርስባቸው በትኩረት እየሰራ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ መድረኩ ተመላሽ ዜጎች ልዩ ልዩ ድጋፍ ስለሚያገኙበትና ከህብረተሰቡ ጋር ሊቀላቀሉ ስለሚችሉበት ሁኔታ የሚመክር መሆኑን አንስተው፤ በተለይም በተበታተነ መልኩ የሚሰጠው ድጋፍ ወደተደራጀና የተቀናጀ አግባብ ለማምጣት ግብዓት የሚገኝበት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ሚኒስቴሩ ለተመላሾች የሚደረገው ድጋፍ ኑሯቸውን በዘላቂነት የሚያቋቁም እንዲሆን ከባለድርሻ አካላት ጋር ያለውን ቅንጅታዊ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል፡፡ በፍትሕ ሚኒስቴር የብሔራዊ ትብብር ጥምረት ፅህፈት ቤት ኃላፊ አብርሃም አያሌው በበኩላቸው፤ ተመላሾቹ ሰብዓዊ መብታቸው እንዲጠበቅ ልዩ ልዩ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለተመላሾቹ ከሚደረገው ዕለታዊ ድጋፍ ባሻገር በዘላቂነት የሚቋቋሙበትን ስልት መቀየስ እንደሚገባ አመላክተዋል፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ችግር ውስጥ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎችን ማገዝ የሁሉም ተቋም ሃላፊነት ነው ያሉት ደግሞ የዓለም አቀፍ የፍልሰት ድርጅት ተወካይ ሚሞሪ መዋሊ ናቸው፡፡ በመሆኑም ተመላሾቹን በዘላቂነት ለማቋቋም እጅ ለእጅ ተያይዞ መስራት እንደሚገባና በዚህ ረገድ የዓለም አቀፍ የፍልሰት ድርጅት በጋራ ለመስራት ቁርጠኛ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ የምክክር መድረኩ ነገም ቀጥሎ እንደሚካሄድ ተገልጿል፡፡
ኢትዮጵያ ስደተኞችን በአካታችነት ተቀብላ ማስተናገዷን አጠናክራ ትቀጥላለች
Jun 13, 2025 64
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ስደተኞችን በአካታችነት ተቀብላ ማስተናገዷን አጠናክራ እንደምትቀጥል ተገለፀ። የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ስደተኞችን በአካታችነት መደገፍን የተመለከተ ከፍተኛ የውይይት መድረክ እያካሔደ ነው። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ የረጅም ጊዜ ታሪክ አላት። ስደተኞችን በአካታችነት በመቀበል የጤና፣ የትምህርትና ሌሎች አገልግሎቶችን በመስጠትና በምጣኔ ሃብት በዘላቂነት ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ በፖሊሲ ደረጃ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች እንደምትገኝ አስረድተዋል። በተመሳሳይ መሰረታዊ በሆኑ አገልግሎቶች በወሳኝ ኩነት እንዲሁም ዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። በትምህርት ዘርፍ በመጀመሪያ ደረጃ፣ በቴክኒክና ሙያ እንዲሁም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የትምህርት አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ ችላለች ብለዋል። በምጣኔ ሃብት ዘርፍም በስራ እድል ፈጠራ በማካተት በዘላቂነት ራሳቸውን የሚችሉበት እድል የተፈጠረ ሲሆን፤ አብዛኞቹ ስደተኞች ይህን እድል እየተጠቀሙበት መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ስደተኞችን ታሳቢ ያደረገ የተቀናጀ እና አካታች አሰራሩን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ስደተኞችን በአካታችነት በዘላቂነት ራሳቸውን እንዲችሉ እያከናወነች ላለው ተግባር ትብብሩን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል። የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ጠይባ ሃሰን እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ስደተኞችን ተቀብላ እያስተናገደች ትገኛለች። መንግስት በዘላቂነት ስደተኞች ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ እየተገበራቸው ላሉ የተለያዩ መርሃ ግብሮች ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የቴክኒክና የገንዘብ ትብብሩን ሊያጠናክር ይገባል ብለዋል። በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ራሚዝ አላክባሮቭ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ለስደተኞች ሁልጊዜም በሯን ክፍት በማድረግ የምትቀበል ሀገር ናት ሲሉ ገልጸዋል። በመሆኑም የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በጀቱን በማሳደግ መንግስት እያከናወነ ያለውን ተግባር ሊደግፍ ይገባል ብለዋል። በውይይቱ የተባበሩት መንግስታት ተወካዮች፣ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ ለስደተኞች የምታደርገውን ድጋፍ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲደግፍ በትኩረት እንሰራለን - ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ
Jun 13, 2025 55
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ስደተኞችን በማስተናገድ እያከናወነች ያለውን መልካም ተግባር ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲያውቅ እና ድጋፍ እንዲያደርግ በትኩረት እንሰራለን ሲሉ የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ ገለጹ። ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲን በብሄራዊ ቤተ መንግስት ተቀብለው በስደተኞች ዙሪያ አነጋግረዋል። የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲን ከውይይቱ በኋላ ዓለም አቀፍ ድጋፍ በተቀዛቀዘበት በዚህ ወቅት ኢትዮጵያ ስደተኞችን ማስተናገዷ የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው፤ የምናደርገውን ድጋፍ አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት የመጡ በርካታ ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ ላይ እንደምትገኝ የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ ይህንኑ መልካም ተግባር ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲደግፍ በትኩረት እንሰራለን ሲሉም ገልጸዋል። ውይይቱን የተከታተሉት የስደተኞች እና ተመላሾች አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ጠይባ ሀሰን እንደገለጹት፤ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ እና በተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲን መካከል የተደረገው ውይይት ውጤታማ ነው። በአሁኑ ወቅት ለስደተኞች የሚደረገው ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ድጋፍ እየቀነሰ መሆኑን ተከትሎ እገዛው በሚጠናከርበት ሁኔታ ላይ ትኩረት አድርገው መወያየታቸውን አንስተዋል፡፡ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀስላሴ በቀጣናው ካለው የሰላም ጉዳይ ጋር ተያይዞ ኢትዮጵያ አሁንም ስደተኞችን እየተቀበለች መሆኗን ማንሳታቸውን ጠቅሰው፤ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ለኮሚሽነሩ መግለጻቸውን አስታውቀዋል፡፡ ኮሚሽነሩ በቀጣይነት ድጋፉ እንደሚጠናከር ለፕሬዝዳንት ታዬ ቃል መግባታቸውን ዋና ዳይሬክተሯ ተናግረዋል፡፡ ኢትየጵያ ስደተኞችን ተቀብላ ማስተናገዷን አድንቀው ለዚህ ተግባሯ ኮሚሽነሩ ትልቅ እውቅና መስጠታቸውንም ጨምረው ገልጸዋል። ኢትየጵያ ዓለም አቀፍ ህጎችን በማክበር ስደተኞችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ህጎችና አሰራሮችን በማውጣት ለዓለም ምሳሌ መሆን የሚችል ስራ እየሰራች ትገኛለች፡፡
በበጀት ዓመቱ ለ315 ዜጎች የተሳካ የዐይን ብሌን ንቅለ ተከላ ህክምና ተከናውኗል
Jun 13, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ለ315 ዜጎች የዐይን ብሌን ንቅለ ተከላ ህክምና በተሳካ ሁኔታ በበጀት ዓመቱ መስጠት መቻሉን የኢትዮጵያ ደምና ሕብረ-ህዋስ ባንክ አገልግሎት አስታወቀ። በማህበረሰቡ ዘንድ እየዳበረ የመጣውን የደም እና የዐይን ብሌን ልገሳ ተግባር ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ አገራዊ ንቅናቄ ሰኔ 7/2017 ዓ.ም እንዲሚካሔድ ተገልጿል። የኢትዮጵያ ደምና ሕብረ ህዋስ ባንክ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ሃብታሙ ታዬ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ የዐይን ብሌን ንቅለ ተከላ ህክምና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል። ቀደም ሲል የዐይን ብሌን ንቅለ ተከላ ህክምና በተለያየ መልኩ ይሰጥ እንደነበረ አስታውሰው፤ ይህ ሁኔታ ህክምናው ወጥነት ባለው መልኩ ተደራሽ እንዳይሆን አድርጎት መቆየቱን ተናግረዋል። በመሆኑም የህክምና አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ እንዲያግዝ ታልሞ ህክምናው በኢትዮጵያ ደምና ሕብረ ህዋስ ባንክ አገልግሎት ስር እንዲሰጥ መደረጉንም ገልጸዋል። ይህም የህክምና አገልግሎቱ ፍትሃዊና ተደራሽ እንዲሆን በማድረግ ረገድ ዓይነተኛ ሚና ማበርከቱንም ጠቁመዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ 315 ለሚሆኑ ዜጎች የዓይን ብሌን ንቅለ ተከላ ህክምና መሰጠቱን ጠቁመው፤ በዚሁ ዓመት እንዲሁ 522 ሰዎች የዓይን ብሌናቸውን ለመለገስ ቃል ገብተዋል ብለዋል። ህክምናው በስፋት እየተሰጠ የሚገኘው በአዲስ አበባ ዳግማዊ ምኒልክ ኮምፕሪሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ሲሆን ህክምናውን በሁሉም የአገሪቷ አካባቢዎች ተደራሽ የማድረግ ስራ ትኩረት ተሰጥቶታል ሲሉም ገልጸዋል። ለአብነትም በሃዋሳ፣ በጎንደር፣ በጅማና መቀሌ ሆስፒታሎች ላይ የዓይን ብሌን ቀዶ ህክምናው እየተሰጠ መሆኑን አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅት የዐይን ብሌን የማንሳት ስራ በሚኒሊክ ሆስፒታል ብቻ የሚሰራ ሲሆን ብሌኑን በመሰብሰብ ለህክምና ተቋማቱ ተደራሽ የሚያደርገው የኢትዮጵያ ደምና ሕብረ ህዋስ ባንክ አገልግሎት መሆኑንም ጠቁመዋል። ይህም የተደራሽነት ጥያቄን ያስከተለ በመሆኑ የዓይን ብሌንን የሚሰበስቡ ተቋማትን ለማስፋት ጥረት እየተደረገ ነው ብለዋል። በዚህ ረገድ በተከናወኑ ተግባራት ጅማ ከተማ ላይ የዓይን ባንክ ተቋምን የማቋቋም ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ባለሙያዎችን መመደብና ማሰልጠን ጨምሮ አገልግሎቱን ለመጀመር የሚያስችል ዝግጅት እየተጠናቀቀ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይ በጀት ዓመት እንደ አገር ተጨማሪ የዓይን ባንክ እንደሚኖር ይጠበቃል ብለዋል። በሌላ በኩል በአሁኑ ወቅት በማህበረሰቡ ዘንድ ደም የመለገስ ተግባር እየዳበረና ባህል እየሆነ መምጣቱን ዋና ዳይሬክተሩ አክለዋል። በአለም አቀፍ ደረጃ በሰኔ ወር የሚከበረውን የዓይን ብሌንና የደም ልገሳ ቀን ምክንያት በማድረግ በኢትዮጵያ ሰኔ 7/2017 አገራዊ ንቅናቄ እንደሚካሔድ ገልጸዋል። “የህይወትና የብርሃን ስጦታ ያበርክቱ ደም ይለግሱ የዐይን ብሌን ይለግሱ” በሚል መሪ ሀሳብ የሚከበረውን ይህን ዓለም አቀፍ በዓል በተለያዩ መረሃ-ግብሮች ለማክበር ዝግጅት ተጠናቋል ብለዋል። በእለቱ በደም ልገሳና በዓይን ብሌን ልገሳ ዙሪያ የማህበረሰብ ንቅናቄ መፍጠር፣ የዓይን ብሌን እንዲሁም በተከታታይ ደም የለገሱ ዜጎች እውቅና የመስጠትና ተግባሩ አመቱን ሙሉ እንዲከወን የማድረግ ስራ ትኩረት እንደሚሰጠው ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የዐይን ብሌን ንቅለ ተከላ ህክምና የተጀመረው በ1995 ዓ.ም ሲሆን እስከ አሁን ለ3ሺህ500 ዜጎች ህክምናው መሰጠቱን ከኢትዮጵያ ደምና ሕብረ ህዋስ ባንክ አገልግሎት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ለመስጠት የሚያስፈልገውን ቅድመ ዝግጅት አጠናቀናል-ዩኒቨርሲቲዎች
Jun 13, 2025 57
አዲስ አበባ፤ሰኔ 6/2017 (ኢዜአ)፦የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ መልቀቂያ ፈተና ለመስጠት የሚያስችላቸውን የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ማጠናቀቃቸው ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ገለጹ፡፡ የ2017 ዓም የ12ኛ ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ከሰኔ 23 እስከ ሀምሌ 8 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ እንደሚሰጥ የትምህርት ምዘናና ፈተናዎች አገልግሎት ይፋ ማድረጉ ይታወቃል። በመላ ሀገሪቱም ከ600 ሺህ በላይ የተፈጥሮ እና የማህበራዊ ሳይንስ ተማሪዎች ፈተናውን በወረቀት እና በበይነ መረብ እንደሚወስዱ የወጣው ፕሮግራም ያሳያል። ኢዜአ ፈተናው ከሚሰጥባቸው መካከል የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ እና የኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲን አነጋግሯል፡፡ የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶክተር ደረጀ እንግዳ የዘንድሮ የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና በወረቀትና በቴክኖሎጂ በተደገፈ መልኩ እንደሚሰጥና ለዚህ የሚረዳ በቂ ዝግጅት በማድረግ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በዩኒቨርሲቲው ከ10 ሺህ በላይ የማህበራዊና የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪዎች ፈተናቸውን እንደሚወስዱ ጠቅሰው ከነዚህ መካከል ከስድስት ሺህ በላይ ተማሪዎች ፈተናውን በበይነ መረብ እንደሚፈተኑ ተናግረዋል። በዚህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ዩኒቨርሲቲው በበይነ መረብ የሚፈትናቸውን ተማሪዎች ቁጥር በእጥፍ ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል። ተማሪዎች ለፈተና ሲመጡ የፋይዳ መታወቂያ መያዝ ግዴታ መሆኑን በመገንዘብ መታወቂያቸውን ይዘው እንዲመጡ አሳስበዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ለማ ጉዲሳ በበኩላቸው በሀገር አቀፍ ፈተናው 7 ሺህ 916 የተፈጥሮ እና የማህበራዊ ሳይንስ ተማሪዎች በዩኒቨርሲቲው እንደሚፈተኑ ተናግረዋል። ዶክተር ለማ አክለውም ከዚህ ቀደም በፈተና አሰጣጡ ላይ ሲያጋጥሙ የነበሩ ተግዳሮቶች እንዳይደገሙ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት አስፈላጊው ዝግጅት መጠናቀቁን ጠቅሰዋል። ዶክተር ደረጀ ሀገር አቀፍ ፈተናው ተማሪዎች በእውቀት ምን ደረጃ ላይ እንዳሉ ራሳቸውን የሚፈትሹበት በመሆኑ ያለምንም መጨናነቅ ራሳቸውን በስነ ልቦና በማዘጋጀት ፈተናውን እንዲወስዱ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። በተለይም በኦንላይን የሚፈተኑ ተማሪዎች ራሳቸውን ለፈተናው ዝግጁ ከማድረግ ባለፈ ከቴክኖሎጂ ጋር በተያያዘ የሚያሳስባቸው ነገር ሊኖር እንደማይገባ አስገንዝበዋል። ዩኒቨርሲቲዎቹ ቀደም ብለው ለፈተናው አጋዥ የሆኑ የመኝታ፣ የጥናት የመመገቢያና እና ሌሎች አስፈላጊ ግብዓቶችን ማመቻቸታቸውን አስታውቀዋል። በቀጣዮቹ ዓመታት ፈተናውን ሙሉ በሙሉ በበይነ መረብ ለመስጠት የሚያስችል ዝግጅት በመደረግ ላይ መሆኑንም ከትምህርት ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ ያሳያል።
አክሲዮን ማህበሩ ባቡር በሚያልፍባቸው አካባቢዎች ስድስት ትምህርት ቤቶች ሊገነባ ነው
Jun 13, 2025 53
ድሬደዋ፣ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፡-የኢትዮ ጅቡቲ ባቡር አክሲዮን ማህበር ባቡር በሚያቋርጣቸው አካባቢዎች ስድስት ትምህርት ቤቶችን ለመገንባት ዝግጅት ማጠናቀቁን ገለጸ። አክሲዮን ማህበሩ የባቡር ሰላምና ደህንነትን በተቀናጀ መንገድ ለመጠበቅ ባቡሩ በሚያልፍባቸው አካባቢዎች ከሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑም ተገልጿል። የኢትዮ ጅቡቲ ባቡር አክሲዮን ማህበር የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ወይዘሮ ሙና አህመድ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ባቡሩ በሚያልፍባቸው ክልሎችና ከተሞች የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች የባቡሩን ደህንነት በመጠበቅ ኃላፊነታቸውን እየተወጡ ነው። እነዚህን ተግባራት ይበልጥ ለማሳደግ አክሲዮን ማህበሩ ባቡሩ በሚያልፍባቸው አካባቢዎች ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች ትምህርት ቤቶችን በመገንባት ማህበራዊ ኃላፊነቱን ይወጣል ብለዋል። አክሲዮን ማህበሩ ከማህበረሰቡ ጋር ተቀናጅቶ በመስራቱ የማህበረሰቡ የባለቤትነት መንፈስ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱንም ተናግረዋል። በዚህም አክሲዮን ማህበሩ ስድስት ዘመናዊ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ገንብቶ ለማህበረሰቡ ያስረክባል ብለዋል። በአክሲዮን ማህበሩ የሚኤሶ-ደወሌ የማህበረሰብ እና ባለድርሻ አካላት ቡድን መሪ ምክትል ኮማንደር ጉልማ ታዬ፤ የባቡር ደህንነትን በአስተማማኝ መንገድ መጠበቅ እንደሚገባ ጠቅሰው ባህላዊ መሪዎችና የአገር ሽማግሌዎች ድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል። ይህንን ሚናቸውን በአግባቡ እንዲወጡ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው በተለይ ባቡሩ በሚጓዝበት መስመሮች የሚኖሩ ወጣቶች የስራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይ አክሲዮን ማህበሩ በሚቀጥለው ዓመት ስድስት ዘመናዊ ትምህርት ቤቶችን ለመገንባት መዘጋጀቱ በጎ እንቅስቃሴ መሆኑንም አመልክተዋል። ''ህብረተሰቡን በማስተባበር የባቡር ደህንነትን እየጠበቅን እንገኛለን'' ያሉት ደግሞ የሶማሌ ኢሳ ማህበረሰብ ባህላዊ መሪና የዑጋዝ ተወካይ አቶ አብዶ ዑመር ናቸው።
በሴቶችና ሕፃናት ላይ የሚደረሱ ጥቃቶችን ለመከላከል ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር ይገባል - ሚኒስቴሩ
Jun 13, 2025 61
ቦንጋ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ በሴቶችና ሕፃናት ላይ የሚደረሱ ጥቃቶችና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ለመከላከል ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር እንደሚገባ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ፆታን መሠረት ያደረገ ጥቃት፣ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችና የሕፃናት ጉልበት ብዝበዛን ለመከላከልና ለማስቆም ያለመ የአመራር ንቅናቄ መድረክ በቦንጋ ከተማ አካሂዷል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሂክማ ኬይረዲን፤ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት ማጠናከር በሴቶችና ሕፃናት ላይ የሚደረሱ ጥቃቶችና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን ለመከላከል መሰረት መሆኑን ገልፀዋል። በተለይ የሕፃናት ጉልበት ብዝበዛና ጥቃቶች ተፈፅመው ሲገኙ ተጠያቂነትን በማስፈን ረገድ የፍትሕ አካላት ሚና የጎላ መሆኑን ጠቁመዋል። በመድረኩ የተገኙት በብልፅግና ፓርቲ የሴቶች ክንፍ አደረጃጀት ዘርፍ ሀላፊ አሰለፈች ታደስ፣ በሴቶችና ሕፃናት ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ለመከላከል የሀይማኖት አባቶችና ሌሎች ተሰሚነት ያላቸው የሕብረተሰብ ክፍሎች ይበልጥ መስራት ይገባቸዋል ብለዋል። ከዚህ በተጓዳኝ የሴቶች አደረጃጀቶችን በማጠናከር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን በማሳደግ ተጋላጭነታቸውን መቀነስ እንደሚገባም ገልጸዋል። ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከር በሴቶችና ሕፃናት ላይ ይደርሱ የነበሩ ጥቃቶችና ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች እየቀነሱ መምጣታቸውን የተናገሩት ደግሞ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ሀላፊ ገነት መኩሪያ ናቸው። በክልሉ ሁሉም ቀበሌዎች የጎጂ ልማዳዊ ድርጊት አስወጋጅ ግብረ ሀይል በማቋቋም በተሰራው ስራ 121 ቀበሌዎችን ከጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶች ነፃ ማድረግ መቻሉንም ተናግረዋል። ለውጤቱም የባለድርሻ አካላት ሚና ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰው በቀጣይም ይህን ቅንጅታዊ አሰራር በማጠናከርና የንቅናቄ ስራዎችን እስከታች ማውረድና መከታተል ላይ ትኩረት እንደሚሰጥ ገልጸዋል። የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ሰብስቤ ሻዎኖ፤ የሴቶችንና ሕፃናትን መብትና ደሕንነት ማስጠበቅ ቅድሚያ የሚጠው ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። ችግሩን ለመከላከል በተደረገው ጥረት የታዩ መሻሻሎችን ለማስቀጠል ተጠያቂነትን የማስፈን ስራ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ቆጭቶ ገብረማሪያም በበኩላቸው የሴቶችና ሕፃናትን መብት ለማስጠበቅ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ ይሰራል ነው ያሉት።
በክልሉ ከ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የአልጋ አጎበር ስርጭት እየተከናወነ ነው
Jun 13, 2025 42
ጂንካ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወቅቱን ዝናብ ተከትሎ ሊከሰት የሚችለውን የወባ በሽታ ለመከላከል ከ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የአልጋ አጎበር ስርጭት እየተከናወነ ይገኛል። የክልሉ ጤና ቢሮ በአሪ ዞን ባይፅማል ቀበሌ የአልጋ አጎበር ስርጭት አስጀምሯል። የክልሉ ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ መና መኩሪያ በወቅቱ እንደገለፁት በክልሉ የወባ በሽታ በሚስተዋልባቸው አካባቢዎች ህብረተሰቡን ያሳተፈ የበሽታ መከላከል ስራ እየተከናወነ ነው። ዛሬ የተጀመረው የአልጋ አጎበር ስርጭት በክልሉ የወባ ተጋላጭ በሆኑ 22 ወረዳዎች ስር ለሚገኙ 325 ቀበሌዎች ተደራሽ እንደሚሆን አመላክተዋል። በመርሃ ግብሩ ከ810ሺህ በላይ የአልጋ አጎበሮች እንደሚሰራጩ ጠቅሰው፥ ከ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አመላክተዋል። በስርጭቱ ህፃናት፣ ነፍሰ-ጡርና የሚያጠቡ እናቶች እንዲሁም አዛውንቶች ቅድሚያ እንደሚሰጣቸው አቶ መና ተናግረዋል። የአልጋ አጎበርን በአግባቡ በመጠቀም ከወባ በሽታ ራስን መከላከል ይገባል ያሉት ደግሞ የክልሉ የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አጉኔ አሾሌ ናቸው። የወባ መከላከል ስራውን ውጤታማ ለማድረግ የአካባቢ ቁጥጥር ስራው ይበልጥ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል። ህብረተሰቡ የወባ በሽታ ምልክቶች ሲመለከት በፍጥነት ወደ ጤና ተቋም በመሄድ ምርመራ ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። የአሪ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ ይሁን ጋሎ በበኩላቸው ዞኑ ለወባ ተጋላጭ ከሆኑ አካባቢዎች አንዱ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ የህብረተሰቡን የወባ ተጋላጭነት ለመቀነስ ህብረተሰቡን ያሳተፈ የወባ መከላከል ስራዎች በትኩረት እየተሰሩ መሆኑን አንስተዋል። ወቅቱ ለወባ ትንኝ መራቢያነት ምቹ በመሆኑ የአካባቢ ቁጥጥር ስራው ከየትኛውም ጊዜ በበለጠ ተጠናክሮ መቀጠሉን አንስተዋል። የአጎበር ስርጭቱ በዞኑ የሚከናወኑ የወባ መከላከል ስራዎችን እንደሚያጠናክር ተናግረዋል። የአልጋ አጎበር ድጋፍ ከተደረገላቸው የባይፅማል ቀበሌ ነዋሪዎች መካከል አርሶ አደር ብዙነሽ ባህሩ፤ በአካባቢያቸው ለወባ ትንኝ መራቢያነት አመቺ የሆኑ ስፍራዎችን በማፅዳት፣ ያቆሩ ቦታዎችን በማፋሰስና በማዳፈን የወባ መከላከል ስራው ላይ ንቁ ተሳትፎ እያደረጉ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ሌላው የቀበሌው ነዋሪ አርሶ አደር ዘውዴ ሺቺ በበኩላቸው በአካባቢው ለወባ ትንኝ መራቢያነት አመቺ የሆኑ ቦታውችን በመለየት ጽዳት እያካሄዱ መሆናቸውን ተናግርዋል። የአልጋ አጎበር ስርጭቱ በክልሉ በሚገኙ 325 ቀበሌዎች እስከ ቀጣይ ሳምንት ተደራሽ እንደሚሆን ቢሮው አስታውቋል። ከአልጋ አጎበር ስርጭቱ ጎን ለጎን የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችም ትኩረት የተስጣቸው ናቸው።