ቀጥታ፡
ማህበራዊ
ባህላዊ ሥርዓቶች ውስጥ ያሉ የአብሮነት ዕሴቶችን ለሰላም ግንባታና ልማት መጠቀም ይገባል
Jan 24, 2026 71
ሸኮ፤ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፦ ባህላዊ ሥርዓቶች ውስጥ ያሉ የአብሮነት እሴቶችን ለሰላም ግንባታና ልማት መጠቀም እንደሚገባ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ተናገሩ። የሸኮ ዘመን መለወጫ እና የምስጋና በዓል "ቲካሻ ቤንጊ" በሸኮ ከተማ በተለያዩ ባህላዊ ሥነ ሥርዓቶች ተከብሯል።   በበዓሉ ላይ የተገኙት ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) እንዳሉት በክልሉ ውስጥ ያሉ ብሔረሰቦች የራሳቸውን ባህል፣ ታሪክና ሥርዓት በማልማት የመጠቀም ልምድ እየተጠናከረ መጥቷል። የሸኮ ዘመን መለወጫ "ቲካሻ ቤንጊ" የመተሳሰብ፣ የአብሮነትና የእርቅ ዕሴቶች እንዳለው ጠቅሰው እነዚህን እና ሌሎች ባህላዊ ሥርዓቶችን ጠብቆ ለሰላም ግንባታና ልማት መጠቀም እንደሚገባ ተናግረዋል። አዝመራ ተሰብስቦ በጎተራ ከተከማቸ በኋላ የጥጋብና የደስታ ዘመን ማሳያ ተደርጎ የሚከበረው "ቲካሻ ቤንጊ" ለአካባቢው ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት መጠናከር ትርጉም ያለው እንዲሆንም መስራት ይገባል ነው ያሉት። ሸኮዎች ተፈጥሮን የሚንከባከቡበትና የባህላዊ ግጭት መፍቻ እውቀቶች ሳይበረዙ ለትውልድ በመሸጋገር ጥቅም እንዲሰጡ መሥራት ያስፈልጋል ሲሉ ተናግረዋል። በክልሉ ባህላዊ ሥርዓቶች ያሏቸውን መልካም እሴቶች ለማጎልበት የክልሉ መንግሥት እኩል የመልማት ዕድል እንደሚያመቻችም ርዕሰ መስተዳደሩ ጠቁመዋል።   የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን "ቲካሻ ቤንጊ" አዲስ እህል በጋራ በመቅመስ የሚከበር የቀደምት አባቶች ሥርዓት ሲሆን ከምርትና ምርታማነት ጋር የተሳሰረ መሆኑንም ገልጸዋል። ተስማምቶ በሰላምና በፍቅር የመኖር ትርክት የሚነገርበት "ቲካሻ ቤንጊ" መከበሩ ጠቃሚ ዕሴቶች ለትውልድ እንዲተላለፉ አስቻይ ሁኔታን ይፈጥራልም ብለዋል። ሸኮዎች ከማኅበራዊ ሥርዓት ባሻገር ከተፈጥሮ ጋር ባላቸው ቁርኝት ጠብቀው ካቆዩት ደን ውስጥ ባለ ልዩ ጣዕም ቡና እና ማር ለማዕከላዊ ገበያ እየቀረበ መሆኑን ተናግረዋል።   የሸኮ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሪ ጉሩሙ በበኩላቸው "ቲካሻ ቤንጊ" በዓል ስላለፈው አዝመራ እና የምርት ሁኔታ ምስጋና፥ ለቀጣይ ልማትም ልመና ለፈጣሪ የሚቀርበበት እንደሆነ ገልጸዋል። በበዓሉ ከጎረቤት ጋር ተሰባስቦ በመብላትና በመጠጣት ከማክበር ባሻገር ስለ አካባቢው መመካከርና ስለ ቀጣይ እርሻ ሥራ መመሪያና ምረቃ ከአባቶች የመቀበል ትውፊታዊ ሥርዓት እንዳለ ጠቅሰዋል። መንግሥት ለባህል ልማት በሰጠው ትኩረት እየተከበረ ባለው "የቲከሻ ቤንጊ" በዓልን በማልማት ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳውን ለማሳደግ እንደሚሰሩ ጠቁመዋል።   ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል አቶ ገዛኸኝ ኡፐም እና ታታሪ ዘካሪያስ ከሩቅም ከቅርብም በአንድ አደባባይ ተሰባስበን ማክበራችን አብሮነታችን ይበልጥ ያጠናክራል ብለዋል።   ተደብቀው የቆዩ ቱባ የባህል ሃብቶችን መጠቀም ከተቻለ የልማትና የተረጋጋ የሰላም ሁኔታን በጋራ መፍጠር እንደሚቻል ተናግረዋል።
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የዜጎችን ተጠቃሚነት እያሳደገ ነው
Jan 24, 2026 184
አሶሳ፤ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡- የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የዜጎችን ችግር በማቃለል የተረጋጋ ኑሮ እንዲመሩ ማስቻሉን የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር ከበደ ይማም ተናገሩ። የኢትዮጵያ ደን ልማት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አቡራሞ ወረዳ ያስገነባቸውን መኖሪያ ቤቶች ለዐቅመ ደካሞች አስረክቧል። በዚሁ ወቅት አቶ ከበደ፤ ለዐቅመ ደካሞች የሚደረገው ድጋፍ መንግሥት ለወገን ደራሽ መሆኑን የሚያረጋግጥበት ብሎም እያከናወነ ያለው ሰው ተኮር ተግባር አካል ነው ብለዋል። ከቤት ግንባታ በጨተማሪ በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ለአካባቢው ማኅበረሰብ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍ ማድረጋቸውንም ጠቁመዋል። የቤቱ ባለቤቶች ፈዳይል ደኑ እና ኪፈያ አሲመድ በበኩላቸው፤ ከዚህ በፊት የነበረው የመኖሪያ ቤታቸው ለመኖሪያ ምቹ እንዳልነበረ አውስተዋል። አሁን የኢትዮጵያ ደን ልማት ምቹ የመኖሪያ ቤት ገንብቶ ስለሰጣቸው መደሰታቸውን እና ቤቶቹ ደረጃቸውን የጠበቁ እና ሙሉ የቤት ዕቃ የተሟላላቸው መሆናቸውን ገልጸዋል።   መንግሥት እያከናወነ ያለው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።
አምስተኛው ሀገር አቀፍ የሥነ-ሕዝብና ጤና ጥናት ለኢትዮጵያ የልማት ዕቅዶች ስኬትና ለፖሊሲ ግቦች መሳካት ቁልፍ ሚና የጫወታል-ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር)
Jan 24, 2026 81
አዲስ አበባ፤ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡-አምስተኛው ሀገር አቀፍ የሥነ-ሕዝብና ጤና ጥናት ለኢትዮጵያ የልማት ዕቅዶች ስኬትና ለፖሊሲ ግቦች መሳካት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) ገለጹ። ‎አምስተኛው ዙር የኢትዮጵያ የሥነ-ሕዝብና ጤና ጥናት የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርት ውጤት ይፋ ማድረጊያ አውደ ጥናት እየተካሔደ ነው። ጥናቱ በእናቶችና ሕፃናት ጤና፣ በቤተሰብ ዕቅድ አጠቃቀም፣ በወሊድ መጠን፣ በጤና ተቋም የመውለድ ተሞክሮ፣ በሕፃናት ክትባት እና በሌሎች ማህበራዊ ጉዳየች ላይ ያተኮረ ሲሆን የተከናወኑ ስራዎች ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸው ተመላክቷል፡፡   የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፥ ጥናቱ ከመደበኛ ስታቲስቲካዊ መረጃነት ባለፈ ለሀገራዊ ብልጽግና ጉዞ ስትራቴጂካዊ ፋይዳ ያለው የፖሊሲ መሣሪያ ነው ብለዋል። ጥናቱ መንግሥት ለልማት ዕቅዶች ስኬታማነት በመረጃ ላይ የተመሠረተ አሠራርን ለመከተል ያለውን ጽኑ ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑንም አክለዋል። ጥናቱ ከጤና ዘርፍ በዘለለ ሰፊ የማክሮ-ኢኮኖሚ ፋይዳ እንዳለው የገለጹት ሚኒስትሯ የ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ አፈጻጸም ያለበትን ደረጃ ለመገምገም እንደሚረዳም ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም በሰው ኃይል ልማት፣ በእናቶችና ሕፃናት ጤና እንዲሁም በሌሎች ማህበራዊ ዘርፎች የታዩ ለውጦችን በትክክል ለመለካት እንደሚያስችል ጠቅሰው፥ ጥናቱ ዓለም አቀፍ መስፈርቶችን የተከተለ መሆኑ ለመረጃው ተዓማኒነትና ለዓለም አቀፍ አጋርነት ወሳኝ መሠረት እንደሚሆንም ገልጸዋል፡፡   የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ በበኩላቸው፥እውነተኛና ጥራት ያለው መረጃ የወደፊቱን የጤና ሥርዓት ውጤታማ ለማድረግ ዋነኛው መሠረት መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ስምንት ዓመታት በዘርፉ ሲተገበሩ የነበሩ መረጃዎች በአብዛኛው በግምትና በትንበያ ላይ የተመሠረቱ መሆናቸውን ጠቅሰው፥ አዲሱ ጥናት ግን ያለንበትን እውነታ በሐቀኝነት ለመገምገም እንደሚረዳና ለቀጣዩ የጤና ዘርፍ የኢንቨስትመንት ዕቅድ እንደ መነሻ እንደሚያገለግል አብራርተዋል። ኢትዮጵያ ባለፉት ስምንት ዓመታት እንደ ኮቪድ-19 እና የአየር ንብረት ለውጥ ያሉ ዓለም አቀፍ ፈተናዎች ቢገጥሟትም፣ ጥናቱ ሳይስተጓጎል እንዲጠናቀቅ ላደረጉ ባለሙያዎችም ምስጋና አቅርበዋል።   የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጌጎ ተስፋዬ (ዶ/ር)፤ የጥናቱ ውጤት ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ የሚያደርግ ዘላቂ የማህበራዊ ጥበቃ ሥርዓት ለመዘርጋትና የሰዎችን ሕይወት ለመለወጥ የሚረዳ ትልቅ መሣሪያ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በከር ሻሌ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ውጤቱ የበርካታ ወገኖች የተቀናጀ ርብርብ ግኝት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ ተዓማኒ መረጃን የማመንጨትና በመረጃ ላይ የተመሠረተ ፖሊሲ የመቅረጽ አቅሟን በተግባር ያረጋገጠችበት መሆኑን ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የሥነ-ሕዝብና ጤና ጥናት ዴስክ ኃላፊና የጥናቱ አቅራቢ አቶ ወርቅነህ ወልደጊዮርጊስ እንደገለጹት፤ ጥናቱ በእናቶችና ሕፃናት ጤና እና በቤተሰብ ዕቅድ አጠቃቀምና በወሊድ መጠን ላይ ያተኮረ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም በጤና ተቋም የመውለድ ተሞክሮ፣ በሕፃናት መቀንጨር እና የሕፃናት ክትባትን ጨምሮ ሌሎች ማህበራዊ ጉዳዮችም የጥናቱ ትኩረት እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡‎ በጥናቱ ውጤት መሠረትም መሻሻሎች እየታዩ መሆኑን ጠቅሰው፥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትም ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን አመላካች መሆኑን ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ምሁራን ለጠንካራ ሀገረ መንግሥት ግንባታ ሚናቸውን በይበልጥ ማጎልበት ይጠበቅባቸዋል
Jan 24, 2026 65
አዲስ አበባ፤ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡- ምሁራን የጋራ ትርክትን በማስረጽ ለጠንካራ ሀገረ መንግሥት ግንባታ ሚናቸውን ማጎልበት እንደሚጠበቅባቸው የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ብርሃነመስቀል ጠና (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ለልጆቻችን የተሻለች ሀገርን ለማስረከብ ምሁራን የወል ትርክትን በማጎልበት ረገድ ትልቅ ኃላፊነት አለብን ሲሉም ገልጸዋል። ምሁራን የነገዋን ኢትዮጵያ የሚቀርጹ ስትራቴጂካዊ መሐንዲሶች መሆናቸውን ገልጸው፤ ትውልድን በመቅረጽና የጋራ መግባባትን በመፍጠር ረገድ ቀዳሚውን ሚና ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ቀደም ሲል የጋራ ማንነትን የሚገነቡ የወል ትርክቶች መዳከማቸው ለሀገረ መንግሥት ግንባታ ትልቅ እንቅፋት ሆኖ መቆየቱን አውስተዋል። ምሁራን በዝምታ ውስጥ በመሆን የታሪክ ተወቃሽ መሆን የለባቸውም፤ በመማር ማስተማር ሂደት ያሉ መምህራንም የተማሪዎችን ስብዕና እና ሀገራዊ ፍቅር በመገንባት ላይ ሊሠሩ ይገባል ብለዋል። የወል ትርክቶች ከታችኛው እስከ ከፍተኛ ትምህርት ድረስ በሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ተካተው ትውልዱ እንዲማርባቸው ማድረግ እንደሚገባም ጠቁመዋል። ምሁራን በትውልድ መካከል ድልድይ በመሆን የጋራ መግባቢያ ነጥቦችን ማፍለቅ እንደሚጠበቅባቸው ጠቁመው፤ ልዩነቶችን ወደ ውበት የሚቀይሩ ጥናታዊ ጽሑፎችንና ውይይቶችን ማበረታታት ይገባቸዋል ብለዋል። የወል ትርክትን ማጎልበት የኅልውና ጉዳይ መሆኑን በመገንዘብ ሁሉም ምሁራን በያሉበት መስክ የድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የፍልሰት ስምምነትን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ሀገራዊ የድርጊት መርሃ ግብር እያዘጋጀች ነው
Jan 24, 2026 53
አዲስ አበባ፤ጥር 16/2018 (ኢዜአ):- ኢትዮጵያ ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ሥርዓታዊ እና ሕጋዊ የፍልሰት አስተዳደርን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ሀገራዊ የትግበራ ዕቅድ እያዘጋጀች መሆኗን የፍትሕ ሚኒስትር ዴኤታ በላይሁን ይርጋ ገለጹ። የዓለም አቀፉ የፍልሰት ስምምነት (Global Compact for Migration) ብሔራዊ የትግበራ ዕቅድ ዝግጅትን በተመለከተ የምክክር መድረክ እየተካሄደ ነው።   እ.ኤ.አ. በ2018 በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የጸደቀው ይህ ስምምነት ፍልሰተኞች ከሚነሱበት እስከ መድረሻቸው ድረስ መብታቸውና ደህንነታቸው ተጠብቆ ዓለም አቀፍ ትብብር እንዲኖር የሚያስችል የመጀመሪያው አጠቃላይ ማዕቀፍ ነው። የፍትሕ ሚኒስትር ዴኤታ በላይሁን ይርጋ በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ የፍልሰት መነሻ፣ መሸጋገሪያና መድረሻ ሀገር በመሆኗ ለስምምነቱ መሳካት ቀደምት ተሳትፎ ስታደርግ መቆየቷን አስታውቀዋል። እ.ኤ.አ. በ2020 ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ የመጀመሪያዋ የስምምነቱ ሞዴል ሀገር በመሆን የመጀመሪያውን ሀገራዊ ሪፖርት ማቅረቧን ጠቅሰዋል። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ኢትዮጵያ በክልላዊና ዓለም አቀፋዊ የስምምነቱ ግምገማ ሂደቶች ላይ በንቃት በመሳተፍ የተቀናጀ ትግበራን ለማስፈን በፌዴራልና በክልል ደረጃ የአቅም ግንባታ ሥራዎችን ስታከናውን መቆየቷን ተናግረዋል። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የሚመራ የመንግሥትና የማህበረሰብ ተሳትፎ ያለበት የቅንጅት መድረክ መቋቋሙን የጠቀሱት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ሀገራዊ የስደተኞች ፖሊሲ ተረቆ ለማፀደቅ በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። አጠቃላይ ሀገራዊ የትግበራ ዕቅድ መዘጋጀቱ በፌዴራልና በክልል ደረጃ ያለውን የዓለም አቀፉ የፍልሰት ስምምነት ትግበራ ለማቀናጀትና ለማፋጠን ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ብለዋል። ይህ ዕቅድ በመንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ አካላት መካከል ጠንካራ ትብብርን እንደሚጠይቅ ተናግረዋል። በዚህ ረገድ ሀገራዊ የትብብር ጥምረት ከዓለም አቀፍ የስደተኞች ድርጅት (አይ ኦ ኤም) ጋር በመሆን ሂደቱን በሥርዓት፣ሁሉንም ባሳተፈ፣ጾታን ባገናዘበና ውጤት ተኮር በሆነ መልኩ ለመምራት የሚያስችል ዕቅድ መዘጋጀቱን አመላክተዋል።   በኢትዮጵያ የዓለም አቀፍ የስደተኞች ድርጅት ተወካይ አቢባቱ ዋኔ በበኩላቸው፤ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በመተባበር ባለፉት ዓመታት የፍልሰት አስተዳደር ሥርዓትን ከኢጋድ እና ከዓለም አቀፍ መርሆዎች ጋር የማጣጣም ሥራ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል። ይህ አዲስ እየተዘጋጀ ያለው ብሔራዊ የትግበራ ዕቅድም ኢትዮጵያ በቀጣይ ዓመታት ለፍልሰት ጉዳይ የሚሰጡ ግቦችን ለመለየት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት ለሚያሳየው ቁርጠኝነትና ባለሙያዎች ለሚያበረክቱት አስተዋጽኦ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ቀልጣፋ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jan 24, 2026 82
ሆሳዕና፤ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቀልጣፋ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ገለፀ፡፡ በክልሉ የመንግሥት አገልግሎትና አሥተዳደር ሪፎርም ትግበራ ማስጀመሪያ መርሐ-ግብር በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡   በዚሁ ወቅት የክልሉ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ገብሬ ጋጌ እንዳሉት፤ የመንግሥት አገልግሎትና አሥተዳደር ሪፎርምን በመተግበር ቀልጣፋ አገልግሎት ተደራሽ እንዲሆን እየተሠራ ነው።   ከዚህ በፊት በመንግሥት አገልግሎት ላይ ይስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን መቅረፍ የሚያስችል ፖሊሲን ከመቅረፅ ጀምሮ ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል አሠራር መዘርጋቱንም ተናግረዋል፡፡ በዚህም በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ሲነሱ የነበሩ የመልካም አሥተዳደር ችግሮችን በመቅረፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ አሠራርን ከመተግበር አንጻር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ወደ ሥራ መግባቱን አንስተዋል። በክልሉ የመንግሥት አገልግሎትና አሥተዳደር ሪፎርም በጤና፣ በፋይናንስ፣ በሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት እና በፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ልማት ቢሮዎች ለመጀመሪያ ዙር ተግባራዊ እንደሚደረግ ጠቁመዋል። የሪፎርሙ መተግበር የአገልግሎት አቅርቦቱን ወጥነት ያለው እንዲሆን ከማድረግ ባሻገር የተገልጋዩን እንግልት እንደሚቀንስ ገልጸው የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።
የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ምክክር የተሻለ አማራጭ ነው
Jan 24, 2026 51
ሆሳዕና፤ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡- የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ምክክር የተሻለ አማራጭ በመሆኑ ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ሥራ ስኬታማነት የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ የሀገር ሽማግሌዎች ተናገሩ። የሲዳማ ክልል የሀገር ሽማግሌ የሆኑት ታደሰ ኮራ እንዳሉት፤ አብሮነትን በማጠናከር የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ምክክርን ባህል ማድረግ የተሻለ አማራጭ ነው። ሀገራዊ ምክክር ዋና ዋና የማያግባቡ ችግሮችን ፈትቶ ሀገራዊ አንድነትን በማምጣት የጋራ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ዓይነተኛ ሚና እንዳለውም አስገንዝበዋል። የሀላባ ዞን የሀገር ሽማግሌ ኢማም ኡልጫፎ አብዶ፤ ምክክርን ባህል ማድረግ ተቀራርቦ በመነጋገር የሚያምን ትውልድ ለመፍጠር የጎላ ሚና እንዳለው አስረድተዋል። ነፍጥን አንግቦ ጫካ በመግባት መፍትሔ እንደማይገኝ ጠቁመው፤ ተሰሚነታቸውን በመጠቀም ሀገራዊ አንድነትን ሊያጠናክሩ በሚችሉ ጉዳዮች ላይ በመሥራት የኮሚሽኑን ተግባር እያገዙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በሀገር ጉዳይ በጋራ መክሮ የወል እሳቤና ትርክት ለመያዝ በኮሚሽኑ የተጀመሩ አሳታፊና አካታች የምክክር ሥራዎች ፋይዳቸው የጎላ ነው ያሉት ደግሞ የሀድያ ዞን የሀገር ሽማግሌ ዳኛ ሰለሞን ኃይሌ ናቸው። ለቆዩ ችግሮች ተቀራርቦ በመወያየት የመፍትሔ አቅጣጫ ለማስቀመጥ ምክክሩ መደላድል እንደሚፈጥርም ተናግረዋል። ልማት እንዲጠናከርና ሀገራዊ ምክክሩም ውጤታማ እንዲሆን እንደ ሀገር ሽማግሌ ሚናቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስተያየት ሰጭዎቹ ለኢዜአ አረጋግጠዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በሀገር አቀፍ ደረጃ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን የመከላከልና የማከም ሥራ ውጤት እያስመዘገበ ነው - የጤና ሚኒስቴር    
Jan 23, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦በሀገር አቀፍ ደረጃ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን የመከላከልና የማከም ሥራ አበረታች ውጤት እያስመዘገበ መምጣቱን የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ። የጤና ሚኒስቴር የብሔራዊ ''ፔን ፕላስ' (ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች) ሕክምና የድርጊት መርሀ ግብር ይፋ አድርጓል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመቆጣጠርና መከላከል ተጨባጭ እርምጃዎች እየተወሰዱ እንደሚገኝ አስረድተዋል።   የሕክምና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነትን በማስፋት የጤና ተቋማትን ደረጃ ለማሻሻል የተወሰዱ እርምጃዎችም ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን በመቀነስ አበረታች ውጤት እያመጣ መሆኑን ገልጸዋል። ከ2026 እስከ 2030 በሚቆየው ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ሕክምና የድርጊት መርሀ ግብር በሀገር አቀፍ ደረጃ በ150 የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች አገልግሎትን ማሳደግ እንደሚያስችል አስታውቀዋል። ይህም ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች የሕክምና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት በማስፋት ማህበረሰቡ በአቅራቢያው እንዲገለገል ያስችላል ብለዋል። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ በበኩላቸው፤ ማህበረሰቡ ተላላፊ ያልሆኑ የበሽታ አይነቶችን ተጋላጭነትን ለመግታት የአመጋገብ ሥርዓቱን በማሻሻል የአካል ብቃት ማዘውተር ይኖርበታል ብለዋል።   በቀጣይም የዜጎችን ተላላፊ ያልሆኑ የበሽታ አይነት ተጋላጭነት ለመቀነስ የሕክምና አገልግሎትን የማሻሻልና ግንዛቤ የማሳደግ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስረድተዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ የስኳርና ደም ግፊት ተላላፊ ያልሆኑ የበሽታ አይነቶች እየጨመረ መምጣቱን ጥናቶች ያሳያሉ ያሉት ደግሞ በጤና ሚኒስቴር የበሽታዎች መከላከልና መቆጣጠር መሪ ሥራ አስፈፃሚ ዶክተር ህይወት ሰለሞን ናቸው።   በዚህም ማህበረሰቡ የአኗኗር ዘይቤውን በማሻሻልና ስፖርታዊ እንቅስቃሴን ባህል በማድረግ ተላላፊ ያልሆኑ የበሽታ ሥርጭቶችን መቆጣጠር እንደሚኖርበት አስገንዝበዋል።
የጤና መድህን ሽፋንን ማሳደግ  የጤና አገልግሎትን በፍትሃዊነት ለማዳረስ ወሳኝ ሚና ይጫወታል 
Jan 23, 2026 126
ድሬዳዋ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የጤና መድህን ሽፋንን ማሳደግ ፍትሃዊ የጤና አገልግሎትን ለማዳረስ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት የኢትዮጵያ ጤና መድህን አገልግሎት አስታወቀ። የ2018 ዓ.ም የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን የአባላት ምዝገባና ዕድሳት ንቅናቄ መድረክ ዛሬ በድሬዳዋ ተጀምሯል።   በንቅናቄ መድረኩ የተገኙት የኢትዮጵያ ጤና መድን አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ያምሮት አንዱአለም፣ በኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የጤና መድህን ሽፋንን ለማሳደግ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በዚህም ባለፈው ዓመት ብቻ ከ63 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስታውሰዋል። የጤና መድህን አገልግሎት ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ፍትሃዊ የጤና አገልግሎት እንዲያገኙ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ተናግረዋል።   ከፍለው መታከም የማይችሉ 17 ሚሊዮን ዜጎችም የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ ለዚህም መንግስት ከ7 ሚሊዮን ብር በላይ ድጎማ ማድረጉን አመልክተዋል። በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር እስካሁን 73 በመቶ ነዋሪዎች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው፣ በቀጣይም ይህን የማላቅ ተግባራት ይከናወናሉ ብለዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የድሬዳዋ የማህበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን የቦርድ ሰብሳቢ ሀርቢ ቡህ በበኩላቸው፤ በከተማዋ የጤና መድህን አገልግሎት ሽፋንን ወደ 95 በመቶ ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል።   የማህበረሰብ አቀፍ የጤና መድህን አገልግሎት ፍትሀዊ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማስፋትና ማህበራዊ ልማትን ለማረጋገጥ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የድሬዳዋ አስተዳደር ጤና ቢሮ ቢሮ ኃላፊ ፅጌረዳ ክፍሌ (ዶ/ር) ናቸው። በንቅናቄው መድረክ ላይ የተሳተፉት የገጠርና የከተማ የጤና ዘርፍ አመራሮች በዘርፉ የተገኙ አበረታች ውጤቶችን ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።
የአፍሪካ ህክምና ግብዓት አምራቾች አውደ ርዕይና ጉባኤ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን አቅም ለማስተዋወቅ የላቀ ሚና አለው
Jan 23, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህክምና ግብዓት አምራቾች አውደ ርዕይና ጉባኤ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን አቅም ለማስተዋወቅ የላቀ ሚና እንዳለው የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ፍሬህይወት አበበ ገለጹ። "ሶስተኛው የአፍሪካ ህክምና ግብዓቶች የንግድ፣ አውደ ርዕይና ጉባኤ 2026" ከመስከረም 25 እስከ 27 ቀን 2019 በአዲስ አበባ ይካሄዳል።   የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ፍሬህይወት አበበ አውደ ርዕይና ጉባኤውን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያስመዘገበችው ስኬትና የግሉን ዘርፍ ለማበረታታት የሰጠችው ትኩረት አውደ ርዕይና ጉባኤውን እንድታዘጋጅ አስመርጧታል። በዝግጅቱ ላይ የህክምና ግብዓት አምራቾች፣ የፋይናንስ አቅራቢዎች፣ የፈጠራ ባለቤቶች፣ ኢንቨስሮች፣ ተመራማሪዎች እና ከ600 በላይ ተሳታፊዎች እንደሚገኙ ተናግረዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተከትሎ በዘርፉ ለተሰማሩ አምራቾች ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የሚከናወኑ ተግባራት መጠናከራቸውንም ገልጸዋል። ከመሰረት ልማት አቅርቦት አኳያ የህክምና ግብዓቶች የሚመረቱባቸው ልዩ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ዝግጁ መሆናቸውንም እንዲሁ። ከዚህ አኳያም ሶስተኛው የህክምና ግብዓት አምራቾች አውደ ርዕይና ጉባኤ ኢትዮጵያ በዘርፉ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት እና አቅሞችን ለማስተዋወቅ መልካም አጋጣሚ የሚፈጥር ነው ብለዋል።   የህክምና ግብዓት አምራቾች ማህበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ታደሰ ተፈሪ በበኩላቸው፤ አውደ ርዕይና ጉባኤው ለሀገር ውስጥ አምራቾች የገበያ ትስስር ለመፍጠር ዓይነተኛ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶችን ለመሳብና የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማሳለጥ ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። የአፍሪካ ህክምና ግብዓት አምራቾች የንግድ፣ አውደ ርዕይና ጉባኤ ሴክሬታሪያት ሊቀ መንበር እንማሬ ሆሳንግ በኢትዮጵያ ባደረጉት ጉብኝት የሀገር ውስጥ አምራቾችን ለማበረታታት እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ለአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ ሊሆኑ እንደሚችሉ መመልከታቸውን ጠቅሰዋል። አውደ ርዕይና ጉባኤው መሰል ስራዎች እንዲጠናከሩ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠሩም ባሻገር በአፍሪካ ያሉ ባለድርሻ አካላትን በማገናኘት ለዘርፉ ዕድገት ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በዞኑ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባራት ተጠናክረው ቀጥለዋል
Jan 23, 2026 99
ነገሌ ቦረና ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ቦረና ዞን በሁሉም ዘርፍ በመከናወን ላይ ያሉ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን የዞኑ ገንዘብ ጽህፈት ቤት ገለጸ። በጽህፈት ቤቱ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ቡድን መሪ አቶ አንድነት አበበ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሰው ተኮር ልማቶች በመከናወን ላይ ናቸው። ለዚህም ተፈጻሚነት አብይ እና የቴክኒክ ኮሚቴ በየደረጃው በማዋቀር በልዩ ትኩረት እየተመራ መሆኑን ገልጸው በአገልግሎቱም በዘጠኝ ወረዳዎች የተውጣጡ ከ200 ሺህ በላይ በጎ ፈቃደኞች እየተሳተፉ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በዚህ ተግባር ካለፈው ክረምት ወዲህ የአረጋዊያን ቤት እድሳትና ግንባታ፣ በከተሞች ጽዳትና ውበት፣ የመጠጥ ውሃ፣ የትምህርት እና የመንገድ መሠረት ልማት፣ ደም ልገሳ፣ አረንጓዴ አሻራ እንዲሁም ሌሎችም ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ስራዎች በስፋት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በተለይ እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴ 877 አዲስ መኖሪያ ቤት ግንባታ እና ከ1 ሺህ በላይ መኖሪያ ቤቶች እድሳት በማድረግ አቅመ ደካሞችንና አረጋዊያንን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል። በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚተዳደሩ ለ15 ሺህ 625 ቤተሰቦች 18 ሚሊዮን ብር የጤና መድህን ዋስትና ኢንሹራንስ በበጎ ፈቃደኞች መሸፈኑንም ገልጸዋል፡፡ እንዲሁም ለበርካታ ሰዎች ነፃ የስኳር፣ የደም ግፊት እና የማህጸን ጫፍ ካንሰር ምርመራ እንዲሁም ነፃ የአይን ሞራ ግርዶሽ ምርመራ እና ህክምና መሰጠቱን አብራርተዋል። ወጣቶች እና ሌሎችም የማህበረሰብ ክፍሎች በበጎ ፈቃድ ስራዎች በመሳተፍ የገንዘብ፣ የጉልበት እና የዕውቀት ተሳትፎ ያደረጉ ሲሆን በዚህም በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ሆነዋል። አሁን ላይም የበጎ ፈቃድ አገልግሎቱን ለማጠናከር እየተሰራ ሲሆን በተለይ በበጋ ወራት የተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ ጥበቃና እንክብካቤ መጀመሩን ገልጸዋል። በተለይ የአካባቢ መራቆትን በዘላቂነት ለመቋቋም እንዲቻል 32 ሚሊዮን ችግኞች የማፍላት ስራ እየተካሄደ መሆኑንም ተናግረዋል።
ጥራት ያለው የጤና መድህን አገልግሎት ተደራሽነትን ለማጠናከር ትኩረት ተሰጥቷል
Jan 23, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ ጥራት ያለው የጤና መድህን አገልግሎት ተደራሽነትን ለማጠናከርና ፍትሐዊ የሕክምና ሥርዓትን ለማስፈን ትኩረት መሰጠቱን የኢትዮጵያ ጤና መድህን አገልግሎት ገለጸ። የኢትዮጵያ ጤና መድህን አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ወርቁ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የጤና መድህን ሥርዓት ዜጎች በሕክምና ወቅት የሚያጋጥማቸውን የክፍያ ስጋት በማስቀረት፣ አካታችና ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኙ ማስቻል ነው፡፡ በዚህም አሁን ላይ በመላ ሀገሪቱ 13 ነጥብ 67 ሚሊዮን አባወራና እማወራዎችን የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ከ63 ሚሊዮን በላይ ዜጎችን የጤና መድህን ተጠቃሚ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል፡፡ በርካቶች የአገልግሎቱን አስፈላጊነት በመረዳት ተጠቃሚ መሆናቸው በጤናው ዘርፍ የእርስ በርስ መደጋገፍና የመረዳዳት ባሕል እንዲጎለብት አድርጓል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት አገልግሎቱ በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች በ1 ሺህ 195 ወረዳዎች ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በ2018 ዓ.ም እየተከናወነ በሚገኘው አዲስ ምዝገባም ተጨማሪ 72 ወረዳዎችን ወደ ሥርዓቱ ለማስገባት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የአገልግሎት አሰጣጡን ይበልጥ በቴክኖሎጂ የተደገፈ፣ ቀልጣፋና ግልጽ ለማድረግም የፋይዳ (ብሔራዊ) መታወቂያ አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡   በጳውሎስ ሆስፒታል ሕክምና ሲከታተሉ ያገኘናቸው አቶ ከማል ሀሰን እና ሱልጣን አብደላ የጤና መድህን ተጠቃሚ በመሆናቸው የቀዶ ሕክምናና የመድኃኒት አገልግሎትን በተፋጠነ መንገድ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ ሥርዓቱ አቅም የሌላቸውን የሕብረተሰብ ክፍሎችን እየታደገ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡   ሌላኛው አስተያየት ሰጭ ሽቱ አበራ እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል ለሕክምና አገልግሎት ከፍተኛ ወጪ ስለሚጠይቅ ተገቢውን ሕክምና ማግኘት አስቸጋሪ ሆኖ ቆይቷል። አሁን ግን በዓመት አንድ ጊዜ በሚከፈል አነስተኛ መዋጮ ከቀላል ሕመም እስከ ከፍተኛ የቀዶ ሕክምና አገልግሎት ማግኘት መቻላቸውን ገልጸዋል። እስካሁን የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ያልሆኑ ዜጎች መንግስት ያመቻቸውን ወሳኝ የሕክምና ዋስትና እንዲጠቀሙ መክረዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የኃይማኖት ተቋማት ለሰላም እሴት ግንባታና ለህዝብ አብሮነት ያላቸውን ሚና የበለጠ ያጠናክራሉ
Jan 23, 2026 89
አሶሳ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የኃይማኖት ተቋማት በኢትዮጵያ የሰላም እሴት ግንባታና ለህዝቦች አብሮነት ያላቸውን ሚና የበለጠ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የኢትዮጵያ ኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ፀኃፊ ቀሲስ ታጋይ ታደለ ገለጹ። በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ከተማ በሰላም እሴት ግንባታ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ ተካሂዷል።   በመድረኩ የተገኙት የኢትዮጵያ ኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ፀሃፊ ሊቀ ትጉኃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ የኃይማኖት ተቋማት ካለባቸው ኃላፊነት መካከል የህዝብ አንድነትና አብሮነትን ማጠናከርና የሰላም እሴቶችን ማጎልበት ዋነኞቹ ናቸው ብለዋል። የኃይማኖት ተቋማቱ ዋና አስተምህሮም ሰላምና ፍቅርን መስበክ፣ መረዳዳትና መተጋገዝን ማጠናከር መሆኑን አንስተዋል። የህዝቦች ግንኙነት የበለጠ እንዲጠናከርና አለመግባባቶችን በውይይትና በንግግር መፍታትም የኃይማኖት ተቋማቱ ዋነኛ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል። የቤንሻንኩል ጉሙዝ ክልል ያለው የኃይማኖት ብዝሃነት በሰላም ግንባታ ላይ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸው፣ በክልሉ የሰፈነውን ሰላም ለማጽናት ተቋማቱ ሚናቸውን የበለጠ ያጠናክራሉ ብለዋል።   የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሠላም ግንባታ ቢሮ ኃላፊ ቢኒያም መንገሻ በበኩላቸው፣ በክልሉ ለተገኘው ሰላም የኃይማኖት ተቋማቱ የማይተካ ሚና እንዳላቸው አንስተዋል። ቀጣይም የክልሉ መንግስትና የጸጥታ አካላት ከኃይማኖት ተቋማት ጋር ጠንካራ ቅንጅት በመፍጠር የሰላም እሴት ግንባታውን የበለጠ ውጤታማ የሚያደርጉ ሥራዎችን እንሰራለን ብለዋል።
ሀገራዊ ምክክሩ ለደረሰበት ወሳኝ ምዕራፍ ስኬታማነት የሁሉም ዜጋ የነቃ ተሳትፎ የበለጠ መጠናከር አለበት
Jan 23, 2026 241
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ለደረሰበት ወሳኝ ምዕራፍ ስኬታማነት የሁሉም ዜጋ የነቃ ተሳትፎ የበለጠ መጠናከር እንዳለበት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች ብሔራዊ መግባባትን ለመፍጠር በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የአጀንዳ ማሰባሰብና ተሳታፊ ልየታ የምክክር መድረክ ማካሄዱ ይታወቃል። ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመገንባት ሀገራዊ ምክክሩ ታሪካዊ ዕድል ነው በቀጣይም ትግራይ ክልል ቀሪ አጀንዳ ማሰባሰብና ተሳታፊ ልየታን በማከናወን ዋናውን ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ለማካሄድ የዝግጅት ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ አስታውቋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የከተማ፣ መሠረተ ልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መሐመድ አብዶ እንዳሉት ምክክር ብሔራዊ መግባባትን ለመፍጠር እጅግ አስፈላጊ አጀንዳ ነው። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽንም በዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ብሔራዊ መግባባትን ለመፍጠር በወሳኝ የምክክር ምዕራፍ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በአጀንዳ ማሰባሰብ፣ በተሳታፊ ልየታና ግብዓት ማሰባሰብ ላይ ኮሚሽኑ ዋናውን ሀገራዊ ምክክር ለማካሄድ የሚበረታታ አስቻይ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክርም ብሔራዊ መግባባትን በመፍጠር አሰባሳቢ ትርክት ለመገንባት ምቹ መደላድል የሚፈጥር ወርቃማ ዕድል መሆኑን ነው ጨምረው ያብራሩት። የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በመጨረሻው ምዕራፍ ብሔራዊ መግባባትን ለመፍጠር ላስቀመጠው ወሳኝ ግብ ስኬታማነት የሁሉም ዜጋ ተሳትፎ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አስገንዘብዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላትም ለሀገራዊ ምክክሩ ሂደት ስኬታማነት የሚጠበቅባቸውን ገንቢ ኃላፊነት እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። ሌላኛዋ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ሙስሊማ ረሽድ በበኩላቸው፤ በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ መፍትሔ ለማበጀት ለምክክር መድረክ ቅድሚያ መስጠት አስፈላጊ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክርም በሃሳብ የበላይነት የተመሰረተ የፖለቲካ ባህል በመገንባት ዘላቂ ሀገራዊ መግባባትን በመፍጠር አንድነትን ለማጽናት ሁነኛ አማራጭ መሆኑን ገልጸዋል። የምክክር ኮሚሽኑ ቀሪ የአጀንዳ ማሰባሰብና ተሳታፊ ልየታ እንዲሁም ዋናውን ሀገራዊ ጉባኤ ለማካሄድ አስፈላጊ የአጀንዳ ልየታና ግብዓት የማሰባሰብ ዝግጅት ላይ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም እንደምክር ቤት አባል ኮሚሽኑ ዓላማውን ለማሳካት የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።  
በኦሮሚያ ክልል በቴክኖሎጂ የተደገፈ ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎት እየተሰጠ ነው
Jan 23, 2026 68
አዳማ፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ)፡- የፍትሕ አገልግሎቱን ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተደራሽ የሚያደርግ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አሠራር እየተተገበረ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ቢሮ ኃላፊ ጉዮ ዋሪዮ ተናገሩ። አዳዲስ የዲጂታል አሠራሮችን ተግባራዊ በማድረግ ዘመናዊና ቀልጣፋ አሠራር መዘርጋቱን ኃላፊው ገልጸዋል። በዚህም ተገልጋዮች ያለ እንግልት ፍትሕ የሚያገኙበት ምኅዳር መፈጠሩንና የአገልግሎት መዘግየትም መቀረፉን ለኢዜአ አረጋግጠዋል። የክስ መዝገቦችን ወደ ዲጂታል በመቀየር አገልግሎቱን በኦንላይን መስጠት መቻሉን፤ ምስክሮችን መጥራት ሳያስፈልግ በዞኖች፣ ከተሞችና ወረዳዎች የፍትሕ ጽሕፈት ቤቶች ቃላቸውን እንዲሰጡ እየተደረገ ነው ብለዋል። በዚህም የፍትሕ አገልግሎቱን ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተደራሽ ማድረግ መቻሉን ገልጸው፤ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። ፖሊስና ዐቃቤ ሕጎች በትብብር የምርመራ መዝገቦችን የማጣራትና ክስ የመመስረት ሥራ እየሠሩ መሆኑንም ጠቁመዋል። ይህን ተከትሎም የመዝገብ ማጥራት ዐቅም እየጨመረ መምጣቱንና የክስ መዝገቦች የጥፋተኝነት ውሳኔ የማሰጠት ዐቅም እያደገ መሆኑን ነው ያስታወቁት። የፍትሕ አሰጣጥና አገልግሎት ተደራሽነት መጓተትና የጥራት ጉድለት ተሻሽሏል ሲሉም ተናግረዋል። በገጠርና በከተሞች በሌብነት የተመዘበረ መሬትን በማስመለስና ሕገ ወጥ አሠራርን ከመከላከል አንፃር ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውንም አንስተዋል። ለበርካታ አገልግሎት ሊውሉ የነበሩ ሕገ ወጥ የመሬት ካርታዎች እንዲመክኑ መደረጉንም ጠቁመዋል።
የሕክምና ቁሳቁስ አቅርቦትን ለማሳለጥ ከመንግስት ተግባር ጎን ለጎን የህዝብና የአጋር አካላት ተሳትፎ ወሳኝ ነው
Jan 23, 2026 109
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የሕክምና ቁሳቁስ አቅርቦትን ለማሳለጥ ከመንግስት ተግባር ጎን ለጎን የህዝብና የአጋር አካላት ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አብዱልቃድር ገልገሎ ገለጹ። በውጭ አገር የሚኖሩ የቦረና ተወላጆች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ለሞያሌ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የህክምና መስጫ ቁሳቁስ ድጋፍ ርክክብ ተደርጓል። የኢትዮጵያ መድኃኒት አቅራቢ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አብዱልቃድር ገልገሎ በዚሁ ወቅት፤ በጤና ተቋማት የሕክምና ግብዓቶችን እና ቁሳቁስ ለማሏላት ከሚከናወኑ ተግባራት ጎን ለጎን የአጋር አካላት ተሳትፎ ለተሳለጠ የህክምና አገልግሎት ዓይነተኛ ሚና አለው።   በሞያሌ ሆስፒታል የታየው የአካባቢው ተወላጆች ተሳትፎ መንግስት የሚሰራውን ስራ የሚያግዝ መሆኑን አመልክተው፤ ለሌሎች አካባቢዎችም እንደ አርአያ የሚወሰድ በጎ ተግባር መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ከሚኒሶታ የመጡት የድጋፉ አስተባባሪ ዶክተር አብዱራህማን ሮኔ እና ከአትላንታ ጆርጂያ የመጡት ዶክተር ዋቆ ዳደቻ የተደረገው ድጋፍ የመንግስትን ጥረት በአጅጉ የሚያግዝ ብሎም ለሆስፒታሉ ተጠቃሚዎች እፎይታን የሚሰጥ ነው ብለዋል፡፡ ድጋፉ ከስዊድን ሂውማን ብሪጅ ከተገኘ ግብረ ሰናይ ድርጅት ጋር የተመቻቸ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከዚህ ቀደምም በቦረና ዞን ተልተሌ ወረዳ ለሚገኘው ተልተሌ ሆስፒታል እና በሜጋ ከተማ ለሚገኘው ሜጋ ሆስፒታል ድጋፍ ማድረጋቸውን አስታውሰዋል፡፡   በቀጣይም ለአሬሮ እና ሌሎች ሆስፒታሎች ተመሳሳይ ድጋፍ ለማድረግ ማቀዳቸውን ጠቁመዋል። የሞያሌ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ አብዲ ኤደን፤ ሆስፒታሉ ለበርካታ ሰዎች አገልግሎት የሚሰጥ በመሆኑ የተደረገው ድጋፍ በቀጣይ የተሻለ አገልግሎት እንዲሰጥ ያግዘዋል ብለዋል። ይህ ተሳትፎ በሌሎች የልማት ስራዎች ላይም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም ነው የገለጹት፡፡   አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል ለተጨማሪ ህክምና ረጅም ርቀት ለመጓዝ ይገደዱ እንደነበር አንስተው፤ የተደረገው ድጋፍ እፎይታን የሚሰጥ እና እንግልትን የሚቀንስ በመሆኑ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
የሥነ ምድር ተመራማሪው ጤናዓለም አየነው(ፕ/ር) ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ
Jan 22, 2026 127
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተፈጥሮና ምዘና ሳይንስ ኮሌጅ የሥነ ምድር ትምህርት ክፍል መምህር እንዲሁም ዓለም አቀፍ የሥነ ምድርና የከርሰ ምድር ውሃ ሳይንቲስት የሆኑት ጤናዓለም አየነው (ፕ/ር) በዛሬው ዕለት ባጋጠማቸው የመኪና አደጋ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ጤናዓለም አየነው (ፕ/ር) በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከ30 ዓመታት በላይ ከማስተማር ባለፈ በዓለም አቀፍ የሥነ ምድር እና ከርሰ ምድር ውሃ ዘርፍ ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል። የከርሰ ምድር ውሃ ላይ ሰፊ እና ጥልቅ ምርምር በማካሄድ የሚታወቁ ሲሆን ከ2 ሺህ በላይ በዓለም አቀፍ ደረጃ የታተሙ የምርምር ሥራዎች ባለቤት ናቸው። ለኢትዮጵያ በከርሰ ምድር የውሃ ዘርፍ ብዛት ያላቸው ችግር ፈቺ የሆኑ ጥናታዊ ምርምሮችን በመስራት ቀዳሚ መሆናቸውንም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ምድር ትምህርት ክፍል የከርሰ ምድር ውሃ ተመራማሪ ሚካኤል ጥላሁን (ፕ/ር)ተናግረዋል።   እስከ ሕልፈተ ሕይወታቸው ድረስ ባስተማሩበት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለተማሪዎቻቸው እንደ አባት መካሪ ለሙያ ባልደረቦቻቸው ደግሞ እንደ ወንድም አጋዥ እንደነበሩም አውስተዋል። የበለስ ኢንጂነሪንግ መስራችና ባለቤት ጤናዓለም አየነው (ፕ/ር) ባለትዳር እና የሁለት ልጆች አባት ነበሩ። የጤናዓለም አየነው (ፕ/ር) ቀብር ሥነ ሥርዓት በነገው ዕለት ከቀኑ 9 ሰዓት በቅድስት ስላሴ ካቴድራል እንደሚፈጸም ፋና ዲጂታል ዘግቧል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በጤናዓለም አየነው (ፕ/ር) ሕልፈት የተሰማውን ሐዘን ገልጾ ለቤተሰቦቻቸው፣ ወዳጅ ዘመዶቻቸው፣ ለሥራ ባልደረቦቻቸውና ተማሪዎቻቸው መጽናናትን ተመኝቷል።
አዋጆቹ ዓለም አቀፍ አሰራርን መሰረት ያደረጉና ኢትዮጵያ ከሀገራቱ ጋር ያላትን ግንኙነት ማጠናከር የሚያስችሉ ናቸው
Jan 22, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ ፍርደኞችን የማስተላለፍ እና የወንጀል ጉዳይ የአሳልፎ መስጠት አዋጆች ዓለም አቀፍ አሰራርን መሰረት ያደረጉና ኢትዮጵያ ከሀገራቱ ጋር ያላትን ግንኙነት ማጠናከር የሚያስችሉ መሆናቸውን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግ እና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እጸገነት መንግስቱ ገለጹ። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 9ኛ መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ተካሂዷል።   በምክር ቤቱ የህግ እና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እጸገነት መንግስቱ እንደተናገሩት በኢትዮጵያና በሕዝባዊት ሪፐብሊክ ቻይና እንዲሁም በኢትዮጵያና በብራዚል ፌዴራላዊ ሪፐብሊክ መንግሥታት መካከል ፍርደኞችን የማስተላለፍ ስምምነቶች ተደርገዋል። በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ እና በደቡብ አፍሪካ ሪፐብሊክ መንግሥታት መካከል በወንጀል የሚፈለጉ ሰዎችን አሳልፎ የመስጠት ስምምነት መደረጉንም ገልጸዋል።   ምክር ቤቱ የኢትዮጵያ መንግሥት ከሀገራቱ ጋር በተደረገው ስምምነት መሠረት ፍርደኞችን የማስተላለፍና የወንጀል ጉዳይ አሳልፎ የመስጠት አዋጆችን መርምሮ በአብላጫ ድምጽ አጽድቋል።   አዋጆቹ ዓለም ዓቀፍ አሰራርን መሰረት ያደረጉ፣ የፍርደኞችን መብት ያከበሩና የማስተላለፉን ስነ-ስርዓት በመከተል የሚፈፀሙ ናቸው ብለዋል። በተለይም ሀገራቱ የብሪክስ አባል ሀገራት በመሆናቸው ከኢትዮጵያ ጋር የንግድ፣ ኢንቨስትመንትና የዲፕሎማሲ ግንኙነት ማጠናከር እንደሚያስችል ተናግረዋል። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል አዋጆቹ ከሀገራቱ ጋር ያለውን ግንኙነት እንደሚያጠናክር ገልጸው፤ ከህግ ተፈጻሚነት አንጻር ጥያቄ አቅርበዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግ እና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እጸገነት መንግስቱ የአዋጆቹ የህግ ተፈጻሚነት ላይ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ሌላው ምክር ቤቱ በሶስት ረቂቅ አዋጆች ላይ የተወያየ ሲሆን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታ መሰረት ኃይሌ አዋጆቹን ለምክር ቤቱ አቅርበዋል።   ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴኤታዋ በኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኩዩሪቲ የማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ፣ የፌዴራል የስፖርት ልማት፣ አስተዳደርና የሕብረት ሥራ ማሕበራት ረቂቅ አዋጆችን አቅርበዋል። በኢትዮጵያ መንግስት እና በኮሪያ ኤክስፖርት-ኢምፖርት ባንክ መካከል የሕክምና መሳሪያ አቅርቦት ፕሮጀክት ምዕራፍ-2 ማስፈፀሚያ የብድር ስምምነት ረቂቅ አዋጅንም አቅርበዋል። አዋጆቹ ከሀገራቱ ጋር ያለውን ንግድና ኢንቨስትመንት ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው የምክር ቤት አባላት ተናግረዋል። ምክር ቤቱ በቀረቡት ረቂቅ አዋጆች ላይ ውይይት በማድረግ ለሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴዎች መርቷቸዋል።    
በጀጎል አለም አቀፍ ቅርስ ውስጥ እየተሰሩ የሚገኙ የኮሪደር ልማት ስራዎች ትውልዱ በታሪክ እንዲታወስ የሚያደርጉ ናቸው - አቶ ኦርዲን በድሪ
Jan 22, 2026 98
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ በጀጎል አለም አቀፍ ቅርስ ውስጥ እየተሰሩ የሚገኙ የኮሪደርና የመልሶ ማልማት ስራዎች እንደ አባቶች ሁሉ ትውልዱ በታሪክ እንዲታወስ የሚያደርጉ ናቸው ሲሉ የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ተናገሩ። ርዕሰ መስተዳድሩ በጀጎል አለም አቀፍ ቅርስ ውስጥ በተለያዩ ስፍራዎች እየተከናወኑ የሚገኙ የኮሪደርና የመልሶ ልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል። በዚህ ወቅትም ርዕሰ መስተዳድሩ አቶ ኦርዲን በድሪ እንደተናገሩት በተለይም በአንደኛ መንገድ፣ በጊዲር መጋላ፣ በጀጎልና በሌሎች ዋና ዋና መንገዶች ውጤታማ የኮሪደርና የመልሶ ልማት ስራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ።   የመስክ ምልከታውም ከዚህ ቀደም የተሰጡ ግብረ መልሶች ተግባራዊ ስለመሆናቸው ለማረጋገጥ ያለመ መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህም አብዛኞቹ ስራዎች ጥራትን፣ ፍጥነትንና ፈጠራን መሰረት ባደረገ መልኩ እየተሰሩ መሆናቸውን ተመልክተናል ብለዋል። አንዱ የኢትዮጵያ መልክ የሆነውና በአለም ቅርስነት በተመዘገበው የጀጎል ቅርስ ውስጥ የተሰሩና እየተሰሩ ያሉ ስራዎች በቅርሱ ላይ ከተጋረጠው አደጋ በመታደግ የአለም አቀፍ ቅርስነቱን ጠብቆ እንዲቆይ ከማስቻል ባሻገር እንደ አባቶች ሁሉ ትውልዱ በሌላ ገድል እንዲታወስ የሚያደርጉ ናቸው። ስራዎቹም የጀጎል ቅርስን የአለም አቀፍ ህያው ሃብት ከመሆን በተጨማሪ የሀገር ውበትና መገለጫነቱን የሚያጎሉ ናቸው ሲሉ ነው የተናገሩት።   እየተከናወኑ በሚገኙ ስራዎችም የተጠናከረ ክትትልና ድጋፍ እየተደረገ ስለመሆኑ ያነሱት ርዕሰ መስተዳድሩ በቀጣይም የተጀመሩ ስራዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ ይሰራል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም