ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
የሹዋሊድ በዓል በዓለም ቅርስነት መመዝገቡ ለቱሪስት ፍሰት መጨመር የጎላ ሚና አለው
Apr 19, 2026 119
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- የሹዋሊድ በዓል በዓለም የማይዳሰስ ቅርስነት መመዝገቡ የቱሪስት ፍሰቱን በመጨመር ለሀገር ገፅታ ግንባታ የጎላ ፋይዳ አለው ሲሉ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለጹ። የሐረሪ ብሔረሰብ በየዓመቱ የሚያከብረው ባህላዊው የሸዋል ኢድ በዓል በአዲስ አበባ ከተማ ተከብራል። በዚሁ ወቅት ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን እንዳሉት፤ የሸዋል ኢድ በዓል የማኅበራዊ እሴቶቻችንን በማጎልበት አንድነት ይበልጥ እንዲጎለብት ከማስቻሉም ባሻገር በሐረሪ ክልል ያሉ የቱሪዝም ፀጋዎችን በማስተዋወቅ የብዝኃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ያስችላል። የሹዋሊድ በተለይም የክልሉ ብሎም የሀገሪቱ የቱሪዝም ዘርፍ እንዲጎለብት ከማድረግ አንፃር የላቀ ጠቀሜታ እንዳለውም ጠቁመዋል። ክልሉ በቱሪዝም ዘርፉ ያለውን እምቅ ዐቅም በመጠቀምም የሕዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ተቋም (ዩኔስኮ) በሕዳር ቀር 2016 ዓ.ም በቦትስዋና በተካሄደው ስብሰባ የሸዋል ኢድ በዓል አከባበርን በማይዳሰስ የሰው ልጅ ቅርስነት መመዝገቡ ይታወሳል።
የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ውድድር የባህልና የወዳጅነት ትስስር የታየበት ነው
Apr 19, 2026 209
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ውድድር የባህል ብልፅግና እና የወዳጅነት ትስስር ጠንክሮ የታየበት ነው ሲሉ የከተማዋ አስተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ሀፍታይ ገብረእግዚአብሔር ገለጹ። የዓለም አትሌቲክስ የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ የአንድ ቀን ውድድር ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ ስታዲየም በስኬት ትናንት ተካሂዷል። ውድድሩ መጠናቀቁን ተከትሎም ለተወዳዳሪ አትሌቶች በአራዳ ፓርክ የእራት ግብዣ ተደርጎላቸዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ሀፍታይ ገብረእግዚአብሔር በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ አዲስ አበባ የታሪክ፣ የእንግዳ ተቀባይነት እና የትስስር ከተማ መሆኗን በተግባር አረጋግጣለች። ከተማዋ እንግዶቿን ተቀብላ ከማስተናገድ ባሻገር፣ እንደ ቤታቸው እንዲሰማቸው ማድረጓን ገልጸዋል። ስፖርት የሚጠይቀውን ከፍተኛ ዲሲፕሊንና መስዋዕትነት እንዲሁም የሚፈጥረውን የተስፋ ስሜት ከተማዋ በሚገባ እንደምትረዳም አስገንዝበዋል። በአዲስ አበባ የተካሄደው ውድድር ከመወዳደሪያነት ባለፈ፣ የወዳጅነት ትስስር የተጠናከረበት፣ የህዝቡ ፍቅር እና የባህል ብልጽግና የታየበት፣ እንዲሁም የከተማዋ ልዩ መንፈስ የተንጸባረቀበት እንደሆነም ጠቁመዋል። አክለውም እንግዶቹ በከተማዋ የሚያሳልፉት እያንዳንዱ ቅጽበት የጋራ ታሪክ አካል እንደሚሆን ገልጸው፤ ቆይታቸው አስደሳች እና የማይረሳ ተሞክሮ እንዲሆንላቸው መልካም ምኞታቸውን አስተላልፈዋል። የዓለም አትሌቲክስ የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ውድድር፣ የኢትዮጵያ አትሌቶች ብቻ የሚሳተፉበት እና ዓለም አቀፍ አትሌቶች የሚሳተፉበት በሚል በሁለት ተከፍሎ ነበር የተካሄደው። የኢትዮጵያ አትሌቶች ብቻ የተሳተፉባቸው የሴቶችና የወንዶች የ10 ሺህ ሜትር፣ እንዲሁም የወንዶች የሦስት ሺህ ሜትር መሰናክል ውድድሮች ትናንት ከእኩለ ቀን በፊት ተካሂደዋል። በውድድሩም በሴቶች 10 ሺህ ሜትር፡ አትሌት ፋንታየ አዳነ፤ በወንዶች 10 ሺህ ሜትር፡ አትሌት ይስማው ድሉ እና በወንዶች ሦስት ሺህ ሜትር መሰናክል አትሌት ገመቹ ጎዳና አንደኛ በመውጣት አሸናፊ ሆነዋል። የዓለም አትሌቲክስ ውድድሩ ከተለያዩ ሀገራት የተውጣጡ አትሌቶች የተሳተፉበት ከመሆኑም በላይ፣ አሸናፊ ለሚሆኑ አትሌቶች ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት እንደሚበረከት ተጠቁሟል።
የሐይቅ እስጢፋኖስ የቅርስና የልማት ሥራዎች አርአያነት ያለው ነው-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 19, 2026 173
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- የሐይቅ እስጢፋኖስ የቅርስና የልማት ሥራዎች አርአያነት ያለው መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ታሪካዊ የሆነውን የሐይቅ አስጢፋኖስ ገዳም መጎብኘታቸውን በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ጠቁመዋል። ከ800 ዓመታት በላይ ካስቆጠሩት ቅርሶች ሙዝየም በተጨማሪ፤ ገዳሙ በፍራፍሬ እና ቡና ልማት፣ በዶሮ እርባታ፣ በጥበበ ዕድ እና በዘይት ምርት የሚያከናውነው ተግባር እጅግ አስደናቂ ነው ብለዋል። የሃይማኖት ተቋማት ለማኅበረሰቡ መንፈሳዊ ብቻ ሳይሆን፤ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ለመፍታት የሐይቅ እስጢፋኖስን መንገድ መከተል እንዳለባቸው ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በተለያዩ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ ዜጎችን ወደ ሀገራቸው በመመለስ የልማት ተሳታፊ እና ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ ነው
Apr 19, 2026 84
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-በኢ-መደበኛ ፍልሰት ወደ መካከለኛው ምስራቅና ሌሎች አካባቢዎች ተጉዘው በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ ዜጎችን ወደ ሀገራቸው በመመለስ፣ በልማት ስራዎች ላይ ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ ገለጹ። መንግሥት ዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲን በመከተል በውጭ ሀገራት የሚኖሩ ዜጎችን መብት፣ ደህንነትና ክብር ለማስጠበቅ ተጨባጭ ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝም ተናግረዋል። ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፥ ዜጎች በሕጋዊ መንገድ ተሰማርተው መስራት የሚችሉበትን ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር ከተለያዩ ሀገራት ጋር የሁለትዮሽ ስምምነቶችን በመፈረም ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያን በውጭ ሀገራት መብታቸው ተከብሮ የላባቸውን ዋጋ እንዲያገኙ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ይሁን እንጂ ሕጋዊ አሰራርን ተከትለው ከመሄድ ይልቅ በኢ-መደበኛ ፍልሰት ከሀገር የሚወጡ ዜጎች መኖራቸውን አስታውሰው፤ ይህም ዜጎችን ለሞት፣ ለአካል ጉዳትና ለሥነ ልቦናዊ ቀውስ የሚዳርግ የተሳሳተ መንገድ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። በመካከለኛው ምስራቅና ሌሎች አካባቢዎች በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ ዜጎችን ወደ ሀገር ቤት ከመመለስ ባለፈ፣ ማህበራዊ አገልግሎቶችን እንዲያገኙ እና ከቤተሰቦቻቸው ጋር እንዲቀላቀሉ እየተደረገ እንደሚገኝም ተናግረዋል። ተመላሾችን በሀገራቸው ሠርተው እንዲለወጡና የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ሥርዓት መዘርጋቱን አንስተዋል። በውጭ ሀገራት ሠርተው የመለወጥ ፍላጎት ያላቸው ዜጎች ራሳቸውን ከተለያዩ ተጋላጭነቶች ለመጠበቅ፣ መንግሥት የዘረጋውን ሕጋዊና መደበኛ የጉዞ ሥርዓት ብቻ ሊከተሉ እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡
የአብሮነት እሴቶችን የበለጠ ለማጎልበት በጋራ መስራት ያስፈልጋል - መስፍን አርዓያ (ፕ/ር)
Apr 18, 2026 297
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ) ፦ የአብሮነት እሴቶችን የበለጠ ለማጎልበት በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ ገለጹ። ‘ከፍልስፍና ወደ ዕለታዊ ተግባር‘ በሚል መሪ ሀሳብ በእውነቱ ሀይሉ (ዶ/ር) የተጻፈው "The Ubuntu Rule of Five" (የኡቡንቱ አምስቱ ደንቦች) የተሰኘ መጽሀፍ የተቋማት ከፍተኛ ሃላፊዎች፣ ምሁራን፣ ከተለያዩ ዘርፍ የተወጣጡ ባለሙያዎች በተገኙበት የመጽሐፍ ምረቃና ውይይት ተካሂዷል። መጽሀፉ የአፍሪካውያን የአብሮነትና የሰብዓዊነት እሴቶች ላይ ባተኮረው የኡቡንቱ ፍልስፍና መርህ ላይ የተመሰረተ መሆኑን ነው። ቀደም ሲል በአማርኛና በአፋን ኦሮሞ ቋንቋዎች ለህትመት መብቃቱም ተገልጿል። አሁን ደግሞ በአፍሪካና በዓለም አቀፍ አንባቢያን ተደራሽ ለማድረግ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ለንባብ መብቃቱ ተጠቅሷል። በመርሃ-ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ እንደገለጹት፤ የአብሮነት እሴቶችን የበለጠ ለማጎልበት በጋራ መስራት ያስፈልጋል ። በሀገሪቱ በተለያዩ ምክንያቶች የተከሰቱ ግጭቶችንና ቁርሾዎችን ለመፍታት መመካከርና መደማመጥ ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል። ሀገራዊ ምክክር የትውልድ ስብራትን ለመጠገን አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው፤ ኢትዮጵያውያን ለመጀመሪያ ጊዜ ለሀገራዊ ምክክር ቀርበዋል ብለዋል። ዛሬ ለምረቃ የበቃው መጽሀፍ የአፍሪካውያን እሴት ከኢትዮጵያውያን እሴቶች ጋር በማጣጣም የተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል። ለሀገራዊ ምክክሩ ሀገር በቀል እሴቶች ጉልህ አስተዋጽኦ ያላቸው በመሆኑ በመጽሀፉ የተካተቱ የሀገሪቷ እሴቶች ለምክክሩ አስፈላጊ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር ዮናስ አዳዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአፍሪካ የኡቡንቱ እሴት ለሀገርና ለዓለም ጠቃሚ የሆነ ሀብት ነው ብለዋል። መጽሀፉ የአብሮነት እሴትን በስፋት ለመተግበር የሚያሰችል መሆኑንም ነው የገለጹት። አርቲስት ደሳለኝ ሀይሉ፤ አብሮነት ለሁላችንም የሚበጅ ነው፤ በኪነ ጥበብ ስራዎቻችን አብሮነትን የሚሰብኩ አስታራቂ ታሪኮችን በስፋት ለህበረተሰቡ ማቅረብ አለብን ሲል ተናግሯል። መጽሀፉ ግለሰባዊና ጠባብ አመለካከትን በማስቀረት አብሮነትን ለማጎልበት የሚቻልባቸውን መንገዶች የሚያመላክት ነው ብሏል። በጅማ ዩኒቨርሰቲ መምህርና "The Ubuntu Rule of Five" የተሰኘው መጽሀፍ ጸሀፊ በእውነቱ ሀይሉ(ዶ/ር)፤ የኡቡንቱ አስተሳሰብ ከቃል ያለፈ ለአፍሪካውያን የተለየ ትርጉም ያለው ለአብሮነትና ለምክክር መሰረት ነው ብለዋል። አስተሳሰቡ ለኢትዮጵያውያን የአንድነት ገመድ ስሪታችን የተቋጨበት ነው ሲሉም ተናግረዋል።
በአስተዳደሩ የሕጻናት መቀንጨርን ለማስቀረት የሥርዓተ ምግብ ሞዴል መንደሮችን በመመስረት እየተሰራ ነው
Apr 18, 2026 282
ሰቆጣ፤ ሚያዚያ10/2018 (ኢዜአ)፡-በዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር የሕጻናት መቀንጨርን ለማስቀረት የሥርዓተ ምግብ ሞዴል መንደሮች መመስረታቸውን የአስተዳደሩ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የስርዓተ ምግብ ባለሙያ ወይዘሮ ወርቅ አያሌው ለኢዜአ እንደገለጹት በብሔረሰብ አስተዳደሩ የሚስተዋለውን የመቀንጨር ችግር ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ነው። መምሪያው ከሰቆጣ ቃል ኪዳን ስምምነት እና ከሌሎች አጋር ድርጅቶች ጋር በመተባበር የህብረተሰቡን የግብርና ምርታማነት በማሳደግ የተመጣጠነ ምግብ የመመገብ ባህሉን ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። እናቶች በጓሮ አትክልት፣ በዶሮና ፍየል እርባታ ሥራ ላይ ተሰማርተው ለልጆቻቸው የተመጣጠነ ምግብ እንዲመግቡ በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ህጻናት ልጆቻቸውን በንጥረ ነገር የበለፀጉ አትክልት፣ ሥጋና ጥራጥሬ ምግቦችን በመመገብ ጤንነታቸው እንዲጠበቅና የተስተካከለ እድገት እንዲኖራቸው የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል። በእዚህም በአስተዳደሩ በሥርዓተ ምግብ ላይ የተሻለ እንቅስቃሴ ባሳዩ 69 ቀበሌዎች 82 ሞዴል መንደሮች መመስረቱን ባለሙያዋ ተናግረዋል። በእያንዳንዱ መንደር 60 የሚያጠቡ ነፍሰ ጡር እናቶችን በማሳተፍ ስርዓተ ምግብን በሚያሳድጉ የጓሮ አትክልትና የእንስሳት እርባታ ሥራዎች ላይ እንዲሰማሩ ተደርጓል ብለዋል። የመንደር ምስረታውን ወደ ሌሎች ቀበሌዎችና ወረዳዎች በማስፋት በሕፃናት ላይ የሚያጋጥመውን የመቀንጨር ችግር ሙሉ በሙሉ ለመፍታት በቀጣይ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራም አስታውቀዋል። በደሃና ወረዳ ዳብጦ ሞዴል መንደር ነዋሪ ወይዘሮ ገነት ደባሽ እንዳሉት በስርዓተ ምግብ ዙሪያ በተሰጣቸው ስልጠና መሰረት የጓሮ አትክልትና የዶሮ እርባታ ሥራ እያከናወኑ ነው። በእዚህም የጓሮ አትክልትና እንቁላልን ከተለያዩ ምግቦች ጋር በማሰባጠር ልጆቼን ለመመገብ ችያለሁ ብለዋል። በተደረገልን የጥቅል ጎመንና የቆስጣ ዘር ድጋፍ በጓሯችን የጓሮ አትክልት አልምተን ለመጠቀም ችለናል ያሉት ደግሞ በአበርገሌ ወረዳ የሳቃ መንደር ነዋሪ ወይዘሮ እሸሽ እሉ ናቸው። የጓሮ አትክልት ልማት ሥራቸው ልጆቻችውን የተመጣጠነ ምግም ለመመገብ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። በኢትዮጵያ በከፍተኛ ሁኔታ የሕጻናት መቀንጨር ችግር ከሚስተዋልባቸው የተከዜ ተፋሰስ አካባቢዎች ውስጥ የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር አንዱ ነው። በሰቆጣ ቃል ኪዳን ስምምነት መሰረት መንግስት በሀገር በቀል መፍትሄ መሰረት ከሁለት ዓመት በታች የሆኑ ሕጻናት ላይ የሚደርሰውን የመቀንጨር ችግር በ2022 ዓ.ም ሙሉ ለሙሉ ለማጥፋት ግብ አስቀምጦ እየሰራ ነው። በዚህም በተከዜና ሌሎች አካባቢዎች ከአምስት ዓመት በታች በሆኑ ህጻናት፣ ነፍሰ ጡርና ወላድ ህጻናት ላይ የሥርአተ ምግብን ለማሻሻል በሚከናወኑ ተግባራት ውጤት እየታየ መምጣቱን መረጃዎች ያሳያሉ። የሰቆጣ ቃል ኪዳን የተመጣጠነ ምግብ አቅርቦትን በማሻሻል የሕጻናትን ጤና፣ እድገትና ልማት ለማረጋገጥ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተም ይገኛል።
አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ከፍታ የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ያበረከቱ አንጋፋ ዲፕሎማት ነበሩ
Apr 18, 2026 267
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ከፍታ የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ያበረከቱ አንጋፋ ዲፕሎማት እንደነበሩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው ገለፁ። አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በሕክምና ሲረዱ ቆይተው መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። የአንጋፋዋ ዲፕሎማት አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ሥርዓተ ቀብር ዛሬ በእንጦጦ ሐመረ ኖህ ኪዳነ ምህረት አንድነት ገዳም መካነ መቃብር ተፈፅሟል። በሥርዓተ ቀብሩ ላይ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የቀድሞው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን፣ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀሙድ አሊ የሱፍ፣ የሀገራት አምባሳደሮችና የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው ለኢዜአ እንዳሉት፤ አምባሳደር ቆንጅት በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ታሪክ ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ ሀገራቸውን ያገለገሉ ብርቱ ዲፕሎማት ነበሩ። አምባሳደሯም በተለያዩ ሀገራት የኢትዮጵያ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር በመሆን፣ በአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት ደግሞ በቋሚ መልዕክተኛነት ሀገራቸውን በታላቅ ኃላፊነት ማገልገላቸውን ገልጸዋል። አምባሳደር ቆንጂት በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሥራ ዘመናቸውም ለበርካታ ዲፕሎማቶች በምሳሌነት የሚጠቀሱ ጠንካራና ታታሪ ዲፕሎማት እንደነበሩ አስታውሰዋል። በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ የከፍታ ጉዞም የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ያበረከቱ አንጋፋና የሀገር ባለውለታ ዲፕሎማት እንደነበሩ አንስተዋል። የዲፕሎማሲ ስራ በሰዓት ሳይገደብ ሙሉ ጊዜና ትኩረት በመስጠት የሚከወን እንደሆነ ያስተማሩም ጭምር መሆናቸው ጠቅሰዋል። በጡረታ ከተገለሉ በኋላም እስከ ህልፈተ ህይወታቸው ድረስ ከአፍሪካ ህብረት ስራዎች በዲፕሎማሲ ዘርፉ ሲያገለግሉ መቆየታቸው ተናግረዋል። አምባሳደር ቆንጂት በህይወት በነበሩበት ወቅት በርካታ ጠንካራ ዲፕሎማቶች ያፈሩ እንደነበሩ ገልፀው፤ በቀጣይም ወጣት ዲፕሎማቶች ከሳቸው ልምድና የህይወት ተሞክሮ ተምረው በመማር ሀገራቸው ለማገልገል ትልቅ መነሳሳት የሚፈጥር ነው ብለዋል። አምባሳደር ቆንጂት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን በኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1950ዎቹ በለጋ እድሜያቸውተቀላቅለው ከዴስክ ኦፊሰርነት እስከ ከፍተኛ አመራርነት ማገልገላቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። በ1932 ዓ.ም በሐረር ከተማ የተወለዱት አምባሳደር ቆንጂት ከዮዲት እምሩ በመቀጠል በኢትዮጵያ ሁለተኛዋ ሴት አምባሳደር በመሆን ሀገራቸውን ለረጅም ዓመታት አገልግለዋል። አምባሳደሯም በኦቶዋ፣ ካይሮ፣ ቴል አቪቭና ቬይና የኢትዮጵያ ሚሲዮኖች በባለሙሉ ስልጣን አምባሳደርነት፤ በአፍሪካ ሕብረትና በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን በቋሚ መልዕክተኛነት ሰርተዋል። ከሰኔ 2009 እስከ መስከረም 2011 ዓ.ም ደግሞ በምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) በመራው የደቡብ ሱዳን የሰላም ስምምነት ልዩ አማካሪ ነበሩ።
በክልሉ ተማሪዎች በሀገር አቀፍ ፈተና ውጤታማ እንዲሆኑ በቅንጅት እየተሰራ ነው
Apr 18, 2026 99
ቦንጋ፤ ሚያዚያ 9/2018 (ኢዜአ)-ተማሪዎች በ12 ክፍል ሀገር አቀፍ ፈተና ውጤታማ እንዲሆኑ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ትምህርት ቢሮ ገለጸ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ትምህርት ቢሮ ምክትል ሀላፊና የመማር ማስተማርና ምዘና ዘርፍ ሀላፊ ደስታ ገነሜ (ዶ/ር) በክልሉ በመደበኛ፣ በማታና በርቀት 15 ሺህ የሚጠጉ ተማሪዎች ሀገር አቀፍ ፈተና እንደሚወስዱ ገልጸዋል። ተማሪዎቹ በሃገር አቀፍ ፈተናው ውጤታማ እንዲሆኑ በፈረቃ እንዲሁም በቅዳሜና እሁድ የማጠናከሪያ ትምህርት መሰጠቱና ማታም ጥምር ቤተመጻህፍት እንዲጠቀሙ መደረጉን አንስተዋል። በትምህርታቸው የተሻሉ ወደ 2 ሺህ የሚጠጉ ተማሪዎች በቋሚነት ትምህርት ቤት ውስጥ አድረው እንዲያጠኑ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም በሚፈለገው መጠን ተማሪዎቻቸውን ወደዩኒቨርሲቲ ላላስገቡ ትምህርት ቤቶች ከአጋር አካላት ጋር በመቀናጀት ልዩ እገዛ እየተደረገላቸው መሆኑን አብራርተዋል። ፈተናው በበይነ መረብ የሚሰጥ በመሆኑ በትምህርት ቤቶች የኢንተርኔት መሰረተ ልማት ዝርጋታና ሌሎች ዝግጅቶች እየተደረጉ ነው ብለዋል፡፡ በሀገር አቀፍ ፈተናው ውጤታማ ለመሆን ዝግጅታቸውን ማጠናከራቸውን የገለጹት ደግሞ የቦንጋ የመሀል ከተማ እና የቢሻው ወልደዮሐንስ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ተማሪዎች ናቸው። በሀገር አቀፍ ፈተናው የተሻለ ውጤት ለማምጣት ዝግጅታቸውን እያጠናከሩ እንደሆነ ከገለጹ ተማሪዎች መካከል የመሀል ከተማ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች ተማሪ እዮብ እምሩ እና ተማሪ ፍቅራለም አቱሞ ይገኙበታል። ትምህርት ቤቱ ከመደበኛ ትምህርት ክፍለ ግዜ በተጨማሪ የሚሰጠውን የማጠናከሪያ ትምህርት በትጋት እየተከታተሉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በግልና ከጓደኞቻቸውጋር በመሆን ጠንክረው እያጠኑ መሆናቸውንና የፈተና ጥያቄዎችን በመስራት ለፈተናው እየተዘጋጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የቢሻው ወልደዮሐንስ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ተግባሩ ተስፋዬ እና ተክልዬ ተሾመ እንዳሉት፣ በውጤታቸው ተመርጠው በትምህርት ቤቱ ውስጥ አድረው እንዲያጠኑ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩ ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ እድል ፈጥሯል ። በትምህርት ቤቱ የሚሰጠው የማጠናከሪያ ትምህርትና በግላቸው የሚያደርጉት ዝግጅት በሀገር አቀፍ ፈተና ጥሩ ውጤት ለማምጣት እንደሚያስችላቸው ገልፀዋል። ከማጠናከሪያ ትምህርት ባለፈ ፈተናው በበይነ መረብ ለመውሰድም የቴክኖሎጂ ድጋፍና የስነ ልቦና ዝግጅት እየተደረገላቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በትምህርት ቤቱ የባዮሎጂ ትምህርት መምህር ቆጭቶ ገብረማሪያም ተፈታኝ ተማሪዎች የተሻለ ውጤት እንዲያስመዘግቡ በማጠናከሪያ ትምህርት ከሚደረገው ድጋፍ ባለፈ በስነልቦናም የማብቃት ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የቢሻው ወልደዮሐንስ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ምክትል ርዕሰ መምህር ጌታቸው መኮንን በበኩላቸው በትምህርት ቤቱ በአዳሪና በመደበኛ 336 ተፈታኝ ተማሪዎች እንዳሉ ጠቅሰው፣ ተማሪዎቹን ለሀገር አቀፍ ፈተና ለማብቃት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ ከመደበኛው ትምህርት በተጨማሪ በተቃራኒ ፈረቃና በቅዳሜና እሁድ የማጠናከሪያ ትምህርት እንደሚሰጥና በሞዴል ፈተናዎች የማለማመድ ስራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ምክትል ርዕሰ መምህሩ አክለውም እንደገለጹት ተማሪዎችን በቴክኖሎጂ ብቁ ማድረግ የሚያስችል ድጋፍና በስነ ልቦናም የማዘጋጀት ስራ እየተከናወነ ይገኛል፡፡
የአምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ሥርዓተ ቀብር ተፈፀመ
Apr 18, 2026 126
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የአንጋፋዋ ዲፕሎማት አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ስርዓተ ቀብር ዛሬ በእንጦጦ ሀመረ ኖህ ኪዳነ ምህረት አንድነት ገዳም መካነ መቃብር ተፈፅሟል። አንጋፋዋ ዲፕሎማት አምባሳደር ቆንጂት ሥነጊዮርጊስ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በሕክምና ሲረዱ ቆይተው መጋቢት 29/2018 ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። አምባሳደር ቆንጂት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርን በ1950ዎቹ በለጋ እድሜያቸው ተቀላቅለው ከዴስክ ኦፊሰርነት እስከ ከፍተኛ አመራርነት ማገልገላቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ አመልክቷል። አምባሳደር ቆንጂት ከዮዲት እምሩ በመቀጠል በኢትዮጵያ ሁለተኛዋ ሴት አምባሳደርም ነበሩ። አምባሳደሯ በኦቶዋ፣ካይሮ፣ ቴል አቪቭና ቬይና በሚገኙ የኢትዮጵያ ሚሲዮኖች ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ሆነው ያገለገሉ ሲሆን፤ በአፍሪካ ህብረትና በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽንም ቋሚ መልዕክተኛ በመሆን ሰርተዋል። ከሰኔ 2009 እስከ መስከረም 2011ዓ.ም ደግሞ ኢጋድ በመራው የደቡብ ሱዳን የሰላም ስምምነት ላይም ልዩ አማካሪ ነበሩ።
በክልሉ በማህበረሰቡ ተሳትፎ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Apr 18, 2026 86
ቡኢ፤ ሚያዚያ 10/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በማህበረሰቡ ተሳትፎ በሁሉም ዘርፎች የላቀ ውጤት ለማስመዝገብ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በህብረተሰብና በባለሀብቱ ተሳትፎ ከ210 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በአዲስ መልክ ተገንብቶ የተጠናቀቀውን የሶዶ ቡኢ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤትን መርቀው አገልግሎት አስጀምረዋል። የትምህርት ዘርፉን መደገፍ የዕድገት ጉዞን ለማፋጠን ያለው ሚና ከፍተኛ መሆኑን በሥነስርዓቱ ላይ ተናግረዋል። መንግሥት በትምህርት ዘርፉ የተስተዋለውን ስብራት ለመጠገን ማህበረሰቡን ያሳተፉ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በባለሀብቱና በማህበረሰቡ ተሳትፎ እንደ አዲስ ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት የተደረገው የሶዶ ቡኢ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የትምህርት ዘርፉን ስኬታማ ለማድረግ የተጀመረው ጥረት አንድ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል። የአካባቢው ባለሀብቶች የትምህርት ዘርፉን ለማጠናከር የጀመሩትን አስተዋጽኦ በሌሎች የልማት ሥራዎችም ሊያጠናክሩ እንደሚገባም ርዕሰ መስተዳድሩ አስገንዝበዋል፡፡ የምስራቅ ጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሙስጠፋ ሀሰን በበኩላቸው ህብረተሰቡ ለአካባቢው ፈጣን እድገት መረጋገጥ በተለያየ መንገድ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ በማህበረሰቡ ተሳትፎ ከ210 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በአዲስ መልክ ተገንብቶ ዛሬ ለአገልግሎት የበቃው የሶዶ ቡኢ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በእውቀት የታነጹ ዜጎችን በማፍራት በኩ አስተዋጾው ከፍተኛ ነው ብለዋል። ተሞክሮውን በሌሎች የዞኑ መዋቅሮች በማስፋት በዘርፉ የተያዘውን ግብ ለማሳካት በትኩረት እንደሚሰራም ገልጸዋል፡፡ ለትምህርት ቤቱን መልሶ ግንባታ ጥሪ ሲቀርብ ባለሀብቶችን በማስተባበር ሀላፊነታቸውን መወጣታችውን የገለጹት ደግሞ ቢትወደድ ባህሩ አብርሃም ናቸው። ትምህርት ቤቱ ከገጠመው ችግር ወጥቶ የመማር ማስተማር ስራን በተሻለ ለማከናውን በሚያስችል መልኩ ደረጃውን ጠብቆ መገንባቱን ጠቁመዋል። ትምህርት ቤቱ በአዲስ መልክ መልሶ መገንባቱ ምቹ የመማሪያ አካባቢን ፈጥሯል ያለችው ደግሞ በትምህርት ቤቱ የ10ኛ ክፍል ተማሪ ቃልኪዳን መርሻ ናት፡፡ ትምህርት ቤቱ ከዚህ ቀደም የነበረበትን የቤተ ሙከራ እና የቤተ መጻህፍት አቅርቦት ችግር ከመፍታት ባለፈ የመማር ማስተማር ሥራውን በተሟላ ሁኔታ ለማከናወን የሚያስችለው መሆኑን ገልጻለች። በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ የፌዴራል፣ የክልልና የምስራቅ ጉራጌ ዞን ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የአካባቢው ተወላጅ ባለሀብቶች፣ ነዋሪዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተሳትፈዋል፡፡
በክልሉ የማይበገር ዘላቂ የጤና ስርአት በመገንባት የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው
Apr 18, 2026 87
ጎንደር ፤ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የማይበገር ዘላቂ የጤና ስርአት በመገንባት የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። በጎንደር ከተማ የሚገኘው የጠዳ ከፍተኛ ትምህርት ጤና ሳይንስ ኮሌጅ በጤናው ዘርፍ በመካከለኛ ደረጃ ሙያተኝነት ያሰለጠናቸውን 445 ባለሙያዎችን ዛሬ አስመርቋል። በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ የተገኙት የክልሉ ጤና ቢሮ ሀላፊ አቶ አብድልከሪም መንግስቱ እንደተናገሩት፤ የክልሉ መንግስት የጤናው ዘርፍ ልማት ለማፋጠን እየሰራ ነው። በዚህም ለማህበረሰቡ የሚሰጠውን የጤና አገልግሎት ጥራት ተደራሽነትና ፍትሀዊነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ነው የገለፁት። በአሁኑ ወቅት ሁለንተናዊ የጤና ሽፋንን በማረጋገጥ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ዘላቂነት ያለው የጤና አገልግሎት እንዲያገኝ በማድረግ በኩል የጤና ሙያተኞች አስተዋጽኦ ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው ነው ብለዋል። ''የዛሬ ተመራቂዎች ሙያችሁን በርህራሄ፣ በታማኝነትና በከፍተኛ የሙያ ስነ- ምግባር በመፈጸም ለህዝብ የገባችሁትን ቃለ መሀላ በተግባር ልታረጋግጡ ይገባል'' ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል። የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው በበኩላቸው ፤የህክምና ሙያ ክቡር የሆነውን የሰው ህይወት የመታደግ ታላቅ ተግባር መሆኑን አመላክተዋል። ኮሌጁ ከመማር ማስተማር ስራው ባሻገር በምርምርና በማህበረሰብ አገልግሎት ዘርፍ ለከተማው የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት ሰፊ አበርክቶ እንዳለው ተናግረዋል። የኮሌጁ ዲን አቶ ዘመነ ሀብቱ በበኩላቸው፤ ኮሌጁ በዛሬው እለት ያስመረቃቸው 445 የመካከለኛ ደረጃ የጤና ባለሙያዎች መሆናቸውን ነው የተናገሩት። ኮሌጁ በፋርማሲ፣ በላቦራቶሪ፣ በጤና መረጃ ስርአትና በጤና ኤክስቴንሽን የትምህርት ዘርፎች ካሰለጠናቸው የዛሬ ተመራቂዎች መካከልም 439 ሴቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። ተመራቂዎች በቀሰሙት የህክምና ሙያ በላቀ ብቃት፣ ስነ-ምግባርና ሰብአዊ ርህራሄ ህዝባቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ አሳስበዋል። በፋርማሲ የትምህርት ክፍል 21 A በማምጣት በከፍተኛ ማእረግ የዋንጫና የሜዳሊያ ተሸላሚ የሆነው እያሱ አሰፋ ፤ በ ቴክኖሎጅ በመታገዝ ሙሉ ጊዜውን ለጥናትና አውሎ ውጤታማ መሆን እንደቻለ ተናግሯል። ከፋርማሲ የትምህርት ክፍል ሶስት ነጥብ 97 በማምጣት በከፍተኛ ማእረግ የሜዳልያ ተሸላሚ የሆነችው አማረች መልኬ፤ በራሴ ጥረትና በወላጆቼ ያልተቆጠበ ድጋፍ ስኬታማ ለመሆን በቅቻለሁ ብላለች። በቀሰመችው ሙያ ሀገርና ህዝቧን በታማኝነት በማገልገል ሙያዊ ኃላፊነቷን ለመወጣት ዝግጁ መሆኑዋን ነው የተናገረችው፡፡
የሃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃን የተቋቋሙበትን የኢትዮጵያ ሕግ የማክበር ግዴታ አለባቸው - ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት
Apr 18, 2026 258
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የሃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃን የተቋቋሙበትን የኢትዮጵያ ሕግ የማክበር ግዴታ እንዳለባቸው የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ገለጹ። "የሃይማኖት ተቋማት የመገናኛ ብዙኃን ለሰላምና አብሮነት" በሚል መሪ ሀሳብ በተዘጋጀው መርሐ ግብር ላይ ከተለያዩ የሃይማኖት ተቋማት የመገናኛ ብዙኃን ተወካዮች ጋር ውይይት ተደርጓል። የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን በመገናኛ ብዙኃን አዋጅ ቁጥር 1238/2013 በተሰጠው ተግባርና ኃላፊነት መሰረት የሃይማኖት ተቋማት የመገናኛ ብዙኃን የይዘት ሥራዎችን በመከታተልና በመገምገም የእርምት እርምጃ ይወስዳል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙሐዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የሃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃን አብዛኞቹ በመርሕ ላይ የተመሰረቱ ሃይማኖታዊ ይዘቶችን ይሰራሉ። ይሁን እንጂ ከሃይማኖት መገናኛ ብዙኃን መካከል ጥቂት እኩይ ዓላማ ያላቸው የሌሎችን በጎ ስራ እያበላሹ ነው ብለዋል። የሃይማኖት መገናኛ ብዙኃን የተመዘገቡት በኢትዮጵያ ሕግ መሆኑን ገልጸው፤ የኢትዮጵያን ሕግ የማክበር ግዴታ አለባቸው ብለዋል። የእምነት ተቋማት ድንበር ተሻጋሪ ናቸው። ነገር ግን ሀገር ድንበርና ሉዓላዊነት ስላላት ያንን ማክበር ተገቢ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የተነሣ በኢትዮጵያ ውስጥ እና ውጭ ያሉ ተመሳሳይ እምነት የሚከተሉ ሰዎች የሚጠየቁት በራሳቸው ሀገር ሕግ ብቻ መሆኑን ተናግረዋል። የሃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃን እንዲቋቋሙ የተጠየቀው ሃይማኖታዊ አስተምህሮን ለማስረፅ ይፈቀድልን በሚል መሆኑን ገልጸው፤ ከተቋቋሙበት ዓላማ ውጭ መስራት ሕግ መተላላፍ ነው ብለዋል። ስለሆነም የሚሻሻል ሕግ አለ ከተባለ ይሻሻልልን ብለው መጠየቅ እንጂ ከሕግ ውጭ መንቀሳቀስ ተገቢ እንዳልሆነ ገልጸዋል። የሃይማኖት ሚዲያዎች ለጋራ ሕዝብና እሴት መጎልበት ያላቸውን ገንቢ ሚና ሲወጡ ሌሎች ጥያቄዎቻቸው እንደሚመለሱ ተናግረዋል። የሃይማኖት መገናኛ ብዙኃን ተቋማት የጋራ ኅብረት በመፍጠር ራሳቸውን በራሳቸው ማረምና የተደራጀ ጥያቄ ማቅረብ እንደሚችሉ ገልጸው፤ መንግሥት ለኅብረቱ መመስረት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል። የሰላም ሚኒስትር መሐመድ ኢድሪስ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ እንደሀገር ለመቀጠሏ የሃይማኖት ተቋማት ሚናቸው የጎላ መሆኑን አንስተዋል። በኢትዮጵያ ሕገ መንግስት በተደነገገው መሰረት ሃይማኖት በመንግሥት ጉዳይ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ እንደማይገባ ገልጸው፤ ነፃነትን ለማፅናት በኃላፊነት መስራት አለባቸው ብለዋል። በኢትዮጵያ የሃይማኖት መገናኛ ብዙኃን መኖራቸው ፀጋ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፤ ለሕዝብ አብሮነትና ሰላም ግንባታ ድርሻው የላቀ መሆኑን ገልጸዋል። የሃይማኖት መገናኛ ብዙኃን የአብሮነት ፀጋዎች የመሆናቸውን ያህል ስህተታቸው ለዘመናት የኖረን የአብሮነት ገመድ ይበጥሳል ብለዋል። በመሆኑም የዜጎችን ሰላምና ደህንነት የማረጋገጥ ሀላፊነት ስላለባቸው፣ ከአውድ ሲወጡ መንግሥት ሕግ እንደሚያስከብር ገልጸዋል። የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ እንደገለጹት፤ የሃይማኖት መገናኛ ብዙኃን ከሃይማኖት ባሻገር የህብረተሰቡን ማህበራዊ እሴቶች ማንጸባረቅ አለባቸው። ሁሉም የሃይማኖት ተቋማት በኢትዮጵያ ሰላም፣ ደህንነትና ሕልውና ላይ ልዩነት ሊኖራቸው እንደማይገባ ገልጸዋል። ሁሉም ሃይማኖቶች ሰላምና መቻቻልን እንደሚሰብኩ ገልጸው፤ ከማህበረሰቡ እሴት ግንባታ ጋር በተያያዙ ጉዳዮች ላይ መስራት አለባቸው ብለዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን ከ370 በላይ የንጹህ መጠጥ ውሃ ተቋማት ተገንብተው አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል
Apr 18, 2026 122
ደብረ ማርቆስ፤ ሚያዚያ 10/2018(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን ባለፉት 9 ወራት ከ370 በላይ የንጹህ መጠጥ ውሃ ተቋማት ተገንብተው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን የዞኑ ውሃ እና ኢነርጂ መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ፍሬው ካሴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተያዘው በጀት ዓመት 499 አነስተኛ የንጹህ መጠጥ ውሃ ተቋማትን ለመገንባት ታቅዶ እየተሰራ ነው። ከዚህ ውስጥም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ ከ370 በላይ የሚሆኑ አነስተኛ የንጹሕ ውሃ ተቋማት ግንባታን በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ለማድረግ መቻሉንም ነው የገለጹት። ቀሪዎቹን ደግሞ እስከ በጀት ዓመቱ መጨረሻ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። ለውሃ ተቋማቱ ግንባታ ከዋለው 150 ሚሊዮን ብር ውስጥ 50 ሚሊዮን ብሩ ከማሕበረሰቡ ቀሪው ደግሞ ከመንግስት የተገኘ መሆኑንም አመልክተዋል። በበጀት ዓመቱ የሚገነቡት የውሃ ተቋማት ሙሉ በሙሉ ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት ሲጀምሩ ከ92 ሺህ በላይ የሚደርሱ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል ። የሚገነቡት የውሃ ተቋማት ሲጠናቀቁ የዞኑን የንጹህ መጠጥ ውሃ ሽፋን አሁን ካለበት ከ48 ነጥብ ሰባት በመቶ ወደ 52 በመቶ ለማሳደግ የሚያስችሉ ናቸው ተብሏል።
በድሬደዋ የሚካሄደው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በማሕበረሰቡ ዘንድ ባህል እየሆነ መጥቷል
Apr 18, 2026 113
ድሬደዋ ፣ ሚያዚያ 9/2018(ኢዜአ)፡- የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የሕብረተሰቡን የመረዳዳትና የመደጋገፍ እሴቶች ይበልጥ እያጠናከረ መምጣቱን የድሬዳዋ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ኮሚሽን ገለፀ፡፡ የኮሚሽኑ የወጣቶችና የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ በሐር አብደላ ለኢዜአ እንደተናገሩት ፤ ባለፈው የክረምት ወራት በተካሔደው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት 320 አዳዲስ ቤቶች ተገንብተው አረጋውያንና አቅመደ ካሞች እንዲረከቡ ተደርጓል። በተጨማሪም 159 የአረጋውያን ቤቶችን በማደስም የተሻለ ኑሮ እንዲመሩ ለማድረግ ተችሏል ነው ያሉት። በክረምቱ ወቅት የተገኙ ውጤቶችን በበጋው ወራትም አጠናክሮ በማስቀጠል 85 ሺ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ ያደረጉ 11 አይነት ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጠቃሜታ ያላቸው ልማቶች መከናወናቸውን ተናግረዋል። ለአብነትም በተጠናቀቁት የክርስትና እና የእስልምና እምነት ተከታዩች የአፅዋማት ወቅት ማዕድ የማጋራት እና ችግረኞችን የመደገፍ ስራዎች በስፋት መከናወናቸውን አንስተዋል። በበጋ ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች ላይ ከ23ሺ በላይ ወጣቶች መሳተፋቸውንም ነው ያመለከቱት። በዋናነትም በደም ልገሳ፣ በማዕድ ማጋራት ፣ ህገ- ወጥ የሰዎች ዝውውርን በመከላከልና ሰላምን በመጠበቅ፣ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን በመከላከልና የጎርፍ መከላከያ መሠረተ ልማቶችን በመጠገን ወሳኝ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል ። የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የችግረኞችን መሠረታዊ ማህበራዊ ችግሮችን ከመፍታት በዘለለ መንፈሳዊና አካላዊ እርካታና ደስታ የሚሰጥ መሆኑን የገለፀው ደግሞ በድሬድዋ አስተዳደር የወረዳ 2 ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አቤል ምስራቅ ነው። ይሄንን መሠረት በማድረግ ባለፈው ክረምትና በተያዘው የበጋ ወራት 39 የአረጋውያንን ቤቶችን በተቀናጀ መንገድ መገንባታቸውንም ጠቅሰዋል ። ከቤቶቹ በተጨማሪ ወጣቶች ማዕድ በማጋራት፣ በፅዳትና ውበት ጥበቃ፣ የአካባቢን ሰላምና ፀጥታ ተደራጅተው በመጠበቅ የላቀ ሚና እየተወጡ መሆናቸውን ገልጸዋል። የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በሺ የሚቆጠሩ ችግረኞችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች በመፍታት ደስተኛ ቤተሰብ ለመፍጠር እያገዘ መሆኑንም አንስተዋል።
በጋሞ ዞን በተፈጥሮ አደጋ ለተፈናቀሉ ወገኖች 2 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ ሰብአዊ ድጋፍ ተደረገ
Apr 18, 2026 111
አርባ ምንጭ፤ ሚያዚያ 10/2018(ኢዜአ)፦ በጋሞ ዞን በተፈጥሮ አደጋ ከቄያቸው ለተፈናቀሉ ወገኖች 2 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ ሰብአዊ ድጋፍ ተደረገ። ዛሬ የሰብአዊ ድጋፉን ያደረጉት የኢትዮጵያ ጤና መድህን አገልግሎት እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ እንዲሁም የጋሞ አብያተ ክርስቲያናት የጋራ ልማት እና የጋሞኛ ቋንቋ ስብከተ ወንጌል ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ናቸው። የኢትዮጵያ ጤና መድህን አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ወርቁ በድጋፍ ርክክቡ ወቅት እንደገለጹት ኢትዮጵያዊያን በመረዳዳትና በመደጋገፍ የዳበረ ባህል አላቸው። በዚህም ተቋሙ 24 ቅርንጫፎችን በማስተባበር በአጠቃላይ 1 ሚሊዮን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያለው የምግብና የቁሳቁስ ድጋፎችን ለጋሞ ዞን አስተዳደር ማስረከባቸውን ተናግረዋል በአደጋው ከቄያቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን መልሶ ማቋቋም ከሁሉም ኢትዮጵያዊያን የሚጠበቅ በመሆኑ ዛሬ የተጀመረው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ እንዲሁም የጋሞ አብያተ ክርስቲያናት የጋራ ልማት እና የጋሞኛ ቋንቋ ስብከተ ወንጌል ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት በጋራ 1 ሚሊዮን ብር የሚያወጣ ሰብአዊ ድጋፍ አድርገዋል። በድጋፉ ብርድ ልብስ፣ የአዋቂና የህፃናት አልባሳት፣ ጫማዎችና ሌሎች ቁሶችም መካተታቸውተመላክቷል። የድጋፉ አስተባባሪ ተወካይ አቶ ጡጋሞ ያልሶ ለወገን ደራሽ ወገን በመሆኑ የተፈናቀሉ ወገኖችን ለመታደግ ድርሻችንን እንወጣለን ብለዋል።
የኃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃን ለሰላምና አብሮነት በኃላፊነት ስሜት መስራት ይገባቸዋል
Apr 18, 2026 330
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የኃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃን ለተከታዮቻቸው ኃይማኖታዊ አስተምህሮን ከማስረጽ ባሻገር ለሀገር ሰላምና አብሮነት በኃላፊነት ስሜት መስራት እንዳለባቸው የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኃይማኖት ዘለቀ ገለጹ። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ባለፉት ሶስት ወራት በኃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃን ላይ ያደረገውን የይዘት ስርጭት ክትትልና ግምገማ ውጤት ይፋ ማድረጊያ መርሀ ግብር አዘጋጅቷል። "የኃይማኖት ተቋማት የመገናኛ ብዙኃን ለሰላምና አብሮነት" በሚል መሪ ሀሳብ በሚካሄደው መርሐ ግብር ላይ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙዓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት፣ የሰላም ሚኒስትር መሀመድ ኢድሪስ፣ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ እና የኃይማኖት ተቋማት የመገናኛ ብዙኃን ተወካዮች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኃይማኖት ዘለቀ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ የኃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙሃን ለህብረተሰቡና ለተከታዮቻቸው ኃይማኖታዊ አስተምህሯቸውን ከማድረስ ባሻገር አብሮነትን፣ መረዳዳትን፣ ፍቅርን፣ ሰላምን፣ ልማትን እና የጋራ ዕሴቶችን በማስረፅ አዎንታዊ አበርክቶ አላቸው። ከለውጡ በፊት በነበሩት የመገናኛ ብዙኃን ሕጎች የኃይማኖት ተቋማት የኃይማኖት መገናኛ ብዙሃን እንዳያቋቁሙ፣ ሕጋዊ ዕውቅና እና ፈቃድ እንዳያገኙ ተከልክለው መቆየታቸውን ገልጸዋል። ይሁን እንጂ ሀገራዊ የሚዲያ ሪፎርም ሲደረግ የመገናኛ ብዙኃን ፖሊሲ እና አዋጅ እንዲሻሻል በማድረግ የኃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃንም በሕግ ዕውቅና እና የብሮድካስት ፈቃድ በማግኘት እንዲንቀሳቀሱ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። የመገናኛ ብዙሃን ባለሥልጣን ከሁሉም የኃይማኖት ተቋማት ጋር በመቀናጀት፤ የተቋማቱ መገናኛ ብዙሃን በሕግ በተሰጣቸው ዕውቅና መሰረት ፈቃድ አውጥተው እንዲንቀሳቀሱ አስፈላጊውን የክትትልና ድጋፍ ስራ ሲያከናውን መቆየቱን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን በመገናኛ ብዙኃን አዋጅ ቁጥር 1238/2013 በተሰጠው ተግባርና ኃላፊነት መሰረት በኃይማኖት ተቋማት መገናኛ ብዙኃን ላይ ላለፉት ሶስት ወራት ያካሄደውን የክትትልና የግምገማ ውጤት ሪፖርት በማቅረብ የጋራ የውይይት መድረክ አዘጋጅቷል ብለዋል። ከ51 በላይ የሚሆኑ የኃይማኖት ቴሌቪዥን ጣቢያዎች ፈቃድ በማግኘት በሥርጭት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው፤ በዲጂታልና በማህበራዊ ሚዲያዎች በኩል ኃይማኖታዊ መልዕክት ለተከታዮቻቸው እንደሚያቀርቡም ገልጸዋል። ይሁን እንጂ ጥቂት የማይባሉት ሕግን የሚተላለፉ፣ ኃይማኖታዊ ዕሴቶችን የሚሸረሽሩ፣ የማህበረሰቡን ባህል እና እሴት የማይወክሉና ሃላፊነት የጎደላቸውን ይዘቶች የሚያሰራጩ እንዳሉም አመልክተዋል። የኃይማኖት መገናኛ ብዙሃን የሀገሪቱን ሕጎች እና የሃይማኖታዊ ዕሴቶችን አክብረው እንዲንቀሳቀሱም ጥሪ አቅርበዋል። በኃይማኖት ሚዲያዎች የሚሰራጩ ይዘቶች ለሁሉም ሀይማኖቶች እና እምነቶች ተገቢ ክብር የሚሰጡ፣ የኃይማኖትና የእምነት ነጻነትን፣ መሰረታዊ ሰብዓዊ መብትን የሚያከብሩ መሆን እንዳለባቸውም አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ኃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ዋና ጸሀፊና የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለስልጣን የቦርድ አባል ቀሲስ ታጋይ ታደለ በበኩላቸው፤ የኃይማኖት ተቋማት ለሀገር ሰላምና አብሮነት የጎላ አበርክቶ እንዳላቸው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የበርካታ ኃይማኖት፣ የጥንታዊ ስልጣኔና የብዝሃ ማንነት ባለቤት መሆኗን ገልጸው፤ የኃይማኖት ተቋማት የዘመናት የሰላም ምንጭ ሆነው መቆየታቸውን አንስተዋል። በመሆኑም መንፈሳዊ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት ብዝሃነትን እንደ ጌጥ በመቁጠር የዜጎችን ትስስርና አንድነት ማጠናከር አለባቸው ብለዋል። ከዚህ ባለፈ ከፈጣሪ የተሰጣቸውን የርህራሄና የፍቅር ትምህርት ወደ ጎን በመተው የጥላቻ ንግግር የሚያራምዱ፣ በኃይማኖት ስም የሚነግዱ አካላት ላይ ሕጋዊ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ በመግለጽ፤ የኢትዮጵያ ሀይማኖት ተቋማት ጉባኤ ተጠያቂነት እንዲሰፍን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል።
ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሰለጠነ የሰው ኃይል በማፍራትና በምርምር ሥራዎች ሚናቸውን እያጠናከሩ ነው
Apr 17, 2026 149
አርባ ምንጭ፤ ሚያዚያ 9/2018 (ኢዜአ)፡-የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሰለጠነ የሰው ኃይል በማፍራትና በምርምር ሥራዎች ያላቸውን ሚና እያጠናከሩ መምጣታቸው ተገለጸ። "ሳይንስ ለዘላቂ ልማት" በሚል መሪ ሃሳብ 12ኛው ዓለም አቀፍ አውደ ጥናት በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የዩኒቨርሲቲው አካዳሚክ ጉዳይ ምክትል ፕሬዚዳንት ቦጋለ ገብረማሪያም (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ለፖሊሲና ስትራተጂ ግብአት የሚሆኑ የምርምር ሥራዎችና የሰለጠነ የሰው ሀይል ማፍራት ላይ አተኩረው እየሰሩ ነው። በእስካሁኑ ሂደትም ተቋማቱ የሚያቀርቧቸው የጥናትና ምርምር ሥራዎች ወደ ተግባር ተቀይረው ዕድገት ለማምጣት እያገዙ መሆናቸውን አመልክተዋል። ዛሬ የተጀመረው አውደጥናትም የዚሁ አካል እንደሆነ ጠቁመው፣ በአውደጥናቱ በሕክምናና ጤና ሳይንስ፣ በተፈጥሮ ቀመር ሳይንስ እና በግብርና ዘርፎች ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጽሑፎች ይቀርባሉ ብለዋል። ጥናታዊ ጽሁፎቹ ለፖሊሲ ግብአት የሚሆኑበትን ሂደት ለማቀላጠፍ አውደጥናቱ መዘጋጀቱንም ጠቁመዋል። በመድረኩ የጥናት ጽሁፍ ካቀረቡት መካከል አበበ መንክር (ዶ/ር) የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የጥናትና ምርምር ሥራዎች ሀገሪቱን ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር ለሚደረገው ጥረት የራሳቸውን ሚና እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል። የትምህርት ተቋማት የሰው ሀይል ከማፍራት ጎን ለጎን ምርምሮችን በማድረግ ለሀገር ልማት አበርክቷቸውን እያጠናከሩ እንደሆነም ጠቁመዋል። ዛሬ በተጀመረው አውደ ጥናትም በሀገሪቱ ለሚስተዋሉ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች መፍትሄ የሚሆኑ የጥናት ውጤቶች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል ብለዋል። ጥናትና ምርምሮቹ የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ምርታማነትን ለማሳደግና በአጭር ግዜ ውስጥ ከተረጂነት ለመውጣት የሚያስችሉ መሆናቸውንም ነው አበበ (ዶ/ር) ያነሱት። ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ በመንግስት ለቴክኖሎጂ ሽግግር የተሰጠውን ትኩረት ማሳደግና የአልሚ ባለሀብቶች እና አርሶ አደሮችን ቅንጅት ማሳደግ ላይ ተጨማሪ ሥራ መስራት ያስፈልጋል ሲሉም ገልጸዋል። ልማትን በዘላቂነት ለማረጋገጥ የምርምር ውጤቶችን ወደ ተግባር የመቀየሩ ሥራ ይበልጥ ሊሰራበት እንደሚገባ ያነሱት ደግሞ ሌላው በአውደ ጥናቱ ላይ የተሳተፉት ተመራማሪ የማነህ ተክላይ (ዶ/ር) ናቸው። እንደእሳቸው ገለጻ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚከናወኑ የጥናትና ምርምር ስራዎች የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር እንዲፈቱ ወደ ተግባር ሊለወጡ ይገባል። ለሁለት ቀናት እየተካሄደ ባለው ዓለም አቀፍ ሲምፖዚየም ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የመጡ ተመራማሪዎች፣ የምርምር ተቋማት እና የመንግስት አካላት እየተሳተፉ ይገኛሉ።
የጤና ነገር …
Apr 17, 2026 266
በዮሐንስ ደርበው ማዲያት ታክሞ ይድናል? እነማንንስ ያጠቃል? የሥነ-ውበት ባለሙያ የሆኑት ዶክተር ሱመያ ኑርሁሴን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ስለማዲያት መንስዔ፣ ምልክቶች እና ሕክምና ሙያዊ ሐሳባቸውን አጋርተዋል። እንደ ባለሙያ ቢደረግ ያሉትንም መክረዋል። • ማዲያት እነማንን ያጠቃል? ማዲያት ማንኛውንም ሰው እንደሚያጠቃ ያነሱት ዶ/ር ሱመያ፤ በብዛት ግን በሴቶች ላይ እንደሚከሰት ያስረዳሉ። በዚህም መሠረት ይላሉ፤ እርግዝና ላይ ያሉ እንዲሁም የወሊድ መከላከያ የሚወስዱ ሴቶች እና ሆርሞናል ቴራፒ ላይ ያሉ ሰዎች በስፋት ለማዲያት ተጋላጭ ናቸው። በተጨማሪም በብዛት ምግብ ማብሰል (ኪችን) ላይ የሚሠሩ ሰዎች ለማዲያት እንደሚጋለጡ ጠቁመዋል። ባብዛኛው ማዲያት የሚያጠቃው በዕድሜ ከ25 ወይም ከ30ዎቹ በላይ የሆኑትን መሆኑንም አንስተዋል። • መንስዔ እንደ ዶክተር ሱመያ ገለጻ፤ ለማዲያት ከሚያጋልጡ መንስዔዎች መካከል ዋነኛው የፀሐይ ጨረር ነው። በተጨማሪም ሆርሞናል ፋክተር (የወሊድ መከላከያ መጠቀም፣ እርግዝና ላይ መሆን፣ ሆርሞናል ቴራፒ መውሰድ) ለማዲያት አጋላጭ መንስዔ ሆነው ይጠቀሳሉ ይላሉ። ጭንቀት እንዲሁም ቆዳን የሚያስቆጡ ነገሮች ለማዲያት አጋላጭ መሆናቸውንም ነው ያብራሩት። • ምልክቶች ማዲያት ቀላ፣ ጠቆር ወይም ደብዘዝ ያለ ቀለም (መልክ) ይዞ ከትንሽ ጀምሮ የሚሰፋ መሆኑን ዶክተር ሱመያ አስገንዝበዋል። ለምሳሌ ይላሉ፤ ጉንጭ ላይ መውጣት ቢጀምር ወደ ሁለቱም ጉንጮች ከዚያም ወደ ግንባር እንዲሁም አገጭ እና አፍንጫ ሊደርስ እንደሚችል ገልጸዋል። በሂደትም የማቃጠል፣ የመቆጥቆጥ እና ማሳከክ ሁኔታ ሊኖረው እንደሚችል ነው ያነሱት። • ሕክምና መንስዔዎቹን ዐውቆ ተገቢውን ጥንቃቄ ማድረግ የሕክምናው አካል መሆኑን ያስገነዘቡት ዶክተር ሱመያ፤ የፀሐይ ጨረር መከላከያዎችን መጠቀም፣ በሕክምና የሚሰጡ መድኃኒቶችን ሳያቋርጡ በትዕግስት መጨረስ (ቶሎ ለውጥ አላየሁበትም ብሎ አለማቋረጥ) እንደሚገባም መክረዋል። የማዲያት ሕክምና ስኬታማነቱ ለሁሉም ሰው በዕኩል ጊዜ እንደማይታይ በመግለጽ፤ እንደተከሰተበት ጊዜ ከሰው ሰው እንደሚለያይ በአጽኦት ተናግረዋል። ለምሳሌ አሉ፤ ዓመታት ያለፉት ማዲያት እና 2 ወራት የሆኑት ሕክምና እኩል ቢጀመርም በተመሳሳይ ጊዜ ላይድኑ እንደሚችሉ አመላክተዋል። ስለዚህ የሌላኛው ድኖ የኔ አልዳነም በሚል ሕክምናን ማቋረጥ ስህተት መሆኑንም ነው ያስረዱት። በሌላ በኩል ማዲያትን አስቀድሞ መከላከል እንደሚቻል አረጋግጠው፤ ይህም የሚሆነው መንስዔዎቹን በማወቅ የማዲያት ተጋላጭ ባለመሆን ነው ብለዋል። ከተቻለ በየሥድስት ወሩ ወይም በየዓመቱ የቆዳ ጤና ምርመራ ማድረግ እና ያለበትን ደረጃ ማወቅም የሚከሰት ችግር ቢኖር እንኳ ሥር ሳይሰድድ በማከም ቶሎ እንዲድን ማድረግ ይቻላል ነው ያሉት።
የኢትዮጵያን የሕክምና ቱሪዝም መዳረሻነት የሚያጎለብት ምቹ ምኅዳር ተፈጥሯል
Apr 17, 2026 384
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ የሕክምና ቱሪዝም መዳረሻነት የሚያጎለብት ምቹ የአሰራር ምኅዳር መፈጠሩን የጤና ሚኒስቴር ገለጸ። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ሳህረላ አብዱላሂ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የጤና ሥርዓቱን በማዘመን ብቃት ያለው የቴክኖሎጂ፣ የሰው ሃብትና የግብዓት አቅም እየተፈጠረ ነው። በሚቀጥሉት አምስት ዓመታትም ኢትዮጵያን ሕክምና ቱሪዝም ማዕከል የሚያደርግ ግብ በማስቀመጥ ምቹ አሰራር ምኅዳር ተፈጥሮ እየተሰራበት መሆኑን ተናግረዋል። የሕክምና ቱሪዝም ተወዳዳሪነትን ለማጎልበትም የጤና ሙያተኞች በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የአቅም ግንባታ ስልጠና እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። የአቅም ግንባታ ስልጠና የሚወስድ ሙያተኞችም ዓለም አቀፍ የሙያ ማረጋገጫ ሰርተፊኬት እንዲያገኙ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። የሕክምና ተቋማት የቴክኖሎጂና ግብዓት የማሟላት ውጤታማ ተግባራትም ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ አስተማማኝ አገልግሎት መስጠት እንደሚያስችል አስረድተዋል። በአዲስ አበባ ብቻ ይሰጡ የነበሩ የካንሰርና ሌሎች የሕክምና አገልግሎቶችን በክልሎች በማስፋት ዜጎች በአቅራቢያቸው አገልግሎት የሚያገኙበት ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል። የጤና ተቋማትን የማዘመን ሥራም ለሕክምና ወደ ውጭ የሚጓዙ ዜጎችን እንግልት በመቀነስ ዓለም አቀፍ የጤና ቱሪዝም ተወዳዳሪነት እያጎለበተ መሆኑን አንስተዋል። የዓለም አቀፍ የሙያ ማረጋገጫ ስታንዳርድ ጸድቆ ወደሥራ መግባቱም የግልና የመንግስት ጤና ተቋማትን አገልግሎት የበለጠ ለማዘመን ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የጤና ተቋማት የሙያ ማረጋገጫ ስታንዳርድም ሀገር ውስጥና የውጭ ሀገራት ዜጎችን የሕክምና አገልግሎት እምነት የሚያጎለብት መሆኑን አስረድተዋል። ይህም በኢትዮጵያ የሚኖሩና ከውጭ የሚመጡ ዜጎችን የጤና አገልግሎት ፍላጎት በማሟላት የሕክምና ቱሪዝም ለማስፋት ገንቢ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የዓለም ጤና ድርጅት ለኢትዮጵያ የምግብና መድኃኒት ባለስልጣን የሰጠው ዕውቅናም የጤና ዘርፍ ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት ወሳኝ አቅም እንደሚፈጥር አብራርተዋል። በቅርቡ ወደሥራ የሚገባው የኢትዮጵያ የመድኃኒትና የምግብ የምርምር ልህቀት ማዕከላት ለጤናው ዘርፍ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን አስታውቀዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያን የጤና ሥርዓት የማዘመን ሥራ በማጠናከር የሕክምና ቱሪዝም ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል።
ከዓለም አቀፍ የፍትሕ ተቋማት ጋር መሥራት የዳኝነትና የፍትሕ ዘርፍ የለውጥ ሥራዎችን ለማጠናከር ይረዳል
Apr 17, 2026 186
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፡- ከዓለም አቀፍ የሕግና ፍትሕ ተቋማት ጋር በጋራ መሥራት በሀገራችን እየተተገበሩ ያሉ የዳኝነትና የፍትሕ ዘርፍ የለውጥ ሥራዎችን በይበልጥ ለማጠናከር የጎላ ድርሻ አለው ሲሉ የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ዓለምአንተ አግደው ገለጹ። በአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ዓለምአንተ አግደው የተመራ ልዑክ በአውሮፓና የኤዥያ ሀገራት የዳኝነትና የፍትሕ ተቋማት የሥራ ጉብኝት አድርጓል። በዚህም በሲንጋፖር፣ በሆንግ ኮንግ፣ በፈረንሳይ እና በኔዘርላንድ የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትን መጎብኘቱን እና ከተቋማት ኃላፊዎች ጋር ውይይት ማድረጉን አቶ ዓለምአንተ ለኢዜአ አስረድተዋል። የጉብኝቱ ዓላማም፤ እንደ ሀገር እና በክልል ደረጃ የተጀመሩ የዳኝነት እና የፍትሕ ዘርፍ የለውጥ ሥራዎችን በይበልጥ እያጠናከሩ ለመሄድ የሚያስችል ልምድ መቅሰም መሆኑን ገልጸዋል። በተጨማሪም በቀጣይ በተመረጡ መስኮች ላይ ከተቋማቱ ጋር በትብብር መሥራት የሚቻልበትን ምቹ መደላድል መፍጠር መሆኑን አስገንዝበዋል። ከጉብኝቱ ጎን ለጎንም አቶ ዓለምአንተ ከሲንጋፖር ዓለም አቀፍ የግልግል ዳኝነት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ግሎሪያ ለም፣ ከዓለም አቀፍ የሽምግልና ማዕከል ሴክሬታሪ ጀነራል ተርሳ ቺንግ (ፕ/ር)፣ ከሆንግ ኮንግ ዓለም አቀፍ የግልግል ዳኝነት ማዕከል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጆዋኒ ላዑ እና ከሆንግ ኮንግ ዓለም አቀፍ የሕግ ማሰልጠኛ ተቋም የዓለም አቀፍ ሕግ ጉዳዮች ኃላፊ ጄምስ ዲንግ (ዶ/ር) ጋር ውይይት አድርገዋል። እንዲሁም በፈረንሳይ ከዓለም አቀፍ የግልግል ዳኝነት ማዕከል ፕሬዚዳንት ክላውዲያ ሰሎሞን፣ ከፓሪስ የግልግል ዳኝነት ማዕከል ፕሬዚዳንት ሃፌዝ ቨርጅ፣ ከዓለም አቀፍ ቋሚ የግልግል ፍርድ ቤት ምክትል ሴክሬታሪያት ጀነራል ጋርት ስኮፊልድ እና ከ ዘ ሄግ ዓለም አቀፍ የሕግ ትምህርት ተቋም ምክትል ሴክሬታሪያት ጄነራል እና ቫሲልቫ እና በግልግል ዳኝነት ላይ ከሚሠሩ የጥብቅና ማኅበራት ተወካዮች ጋር መክረዋል፡፡ በዚሁ ወቅትም አቶ ዓለምአንተ፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢትዮጵያ የተጀመሩ እና የተሠሩ ሰፋፊ የሕግ ማዕቀፍ ማሻሻያ እና ሁለንተናዊ የተቋም ግንባታ የለውጥ ሥራዎችን አብራርተዋል። በተጨማሪም ተደራሽ እና ውጤታማ የዳኝነት ሥርዓት ለመገንባት እና ፍርድ ቤቶችን ለማዘመን እየተሠሩ ያሉ ሥራዎችን አስረድተዋል። በተለይም አማራጭ ያለመግባባት መፍቻ ሥርዓቶችን ለማጠናከር እንደ ሀገር እየተሠሩ ያሉ ሥራዎችን ጨምሮ በፍርድ ቤቶች የተመዘገቡ የለውጥ ሥራ ውጤቶችን እና የቀጣይ ትኩረት አቅጣጫዎችን ብሎም የትብብር መስኮችን አንስተዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት እና የዓለም አቀፍ ተቋማት መቀመጫ እንዲሁም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዓለም አቀፍ ትስስር የፈጠረላት በመሆኑ የትልቅ ኢኮኖሚ ባለቤት እና በሰፋፊ የኢኮኖሚ፣ የሕግና የተቋም ግንባታ ማሻሻያ ውስጥ እያለፈች በዚህም ሀገሪቱን የግልግል ዳኝነት ማዕከል ለማድረግ ለተጀመረው ሥራ አስቻይ ሁኔታዎች መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይም አማራጭ ያለመግባባት መፍቻ ሥርዓቶችን ለማጠናከር በተያዘው የዳኝነትና የፍትሕ ዘርፍ ዕቅድ ላይ ዓለም አቀፍ የሕግና የፍትሕ ተቋማት እንዲሁም ሀገራቱ በትብብር መሥራታቸው የጎላ ጠቀሜታ እንዳለው በአጽንዖት ገልጸዋል። የዓለም አቀፍ ተቋማቱ አመራሮች በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ የዳኝነትና የፍትሕ ዘርፍ እንዲሁም በአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተጀመሩ የለውጥ ሥራዎችን ውጤታማነት አድንቀዋል። በቀጣይም በባለሙያ ዐቅም ግንባታ፣ በቴክኒክ ድጋፍ እና ልምዶችን በማጋራት ረገድ በትብብር ለመሥራት ያላቸውን ፍላጎት ለልዑኩ አረጋግጠዋል።