ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ኢትዮጵያ መድን ከሸገር ከተማ ጋር ተስተካካይ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል
Dec 10, 2025 42
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ መድን ከሸገር ከተማ ይጫወታሉ። ጨዋታው ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ መድን በሊጉ ካደረጋቸው ስምንት ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን ሲያሽንፍ ሶስት ጊዜ ደግሞ ተሸንፏል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ጎሎችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በዘጠኝ ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ሸገር ከተማ በበኩሉ በሊጉ ካከናወናቸው ስምንት ጨዋታዎች መካከል በሶስቱ ድል ሲቀናው ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። ሶስት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያገናኝ ሰባት ግቦች ተቆጥረውበታል። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በ12 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው ኢትዮጵያ መድን ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ሸገር ከተማ ደግሞ በአሸናፊነቱ ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው። መርሃ ግብሩ ኢትዮጵያ መድን በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ከግብጹ ፒራሚድስ ጋር በነበረው የማጣሪያ ጨዋታ ምክንያት የተራዘመ መሆኑን የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
ተጠባቂው የሪያል ማድሪድ እና የማንችስተር ሲቲ የሻምፒዮንስ ሊግ ፍልሚያ
Dec 10, 2025 44
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዛሬ ዘጠኝ ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 5 ሰዓት ላይ ሪያል ማድሪድ እና ማንችስተር በበርናባው ስታዲየም የሚያገናኘው ጨዋታ የእግር ኳስ ቤተሰቡን ትኩረት ስቧል። ሪያል ማድሪድ በ12 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ማንችስተር ሲቲ በ10 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ15ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 14 ጨዋታዎች ማንችስተር ሲቲ አምስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሪያል ማድሪድ አራት ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ሁለቱም ቡድኖች በጨዋታዎቹ ላይ በተመሳሳይ 24 ግቦችን አስቆጥረዋል። ቡድኖቹ በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ2024/25 የውድድር ዓመት ነው። በጥሎ ማለፉ ተገናኝተው ሪያል ማድሪድ ማንችስተር ሲቲን 3 ለ 1 አሸንፏል። የስፔኑ ቡድን 15 ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ በስኬት ያሸበረቀ ታሪክ አለው። ማንችስተር ሲቲ አንድ ጊዜ ዋንጫ አንስቷል። ሪያል ማድሪድ እና ማንችስተር ሲቲ ባለፉት ዓመታት በአውሮፓ መድረክ እያደረጉት ያለው ፉክክር የዛሬውን ጨዋታ ትኩረት እንዲያገኝ አድርጎታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ክለብ ብሩዥ ከሊግ ፎርማቱ መሪ አርሰናል፣ አትሌቲኮ ቢልባኦ ከወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ፒኤስጂ፣ ጁቬንቱስ ከፓፎስ፣ ቤኔፊካ ከናፖሊ፣ ባየር ሌቨርኩሰን ከኒውካስትል ዩናይትድ እና ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ከቦዶ ግሊምት በተመሳሳይ ከምሽቱ 5 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ካራባግ ከአያክስ እና ቪያሪያል ከኮፐንሃገን ይጫወታሉ።
ሊቨርፑል ኢንተር ሚላንን አሸነፈ
Dec 10, 2025 68
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሊግ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጠባቂ ጨዋታ ሊቨርፑል ኢንተር ሚላንን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በጁሴፔ ሜኤዛ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዶምኒክ ስቦዝላይ በ88ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት አስቆጥሯል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ሊቨርፑል በ12 ነጥብ ደረጃውን ወደ ስምንት ከፍ አድርጓል። ኢንተር ሚላን በተመሳሳይ 12 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በሌላኛው ጨዋታ አትላንታ ቼልሲን 2 ለ 1 አሸንፏል። ጂያንሉካ ስካማካ እና ቻርልስ ዲ ኬቴላሬ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጆአኦ ፔድሮ ለቼልሲ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ ስላቪያ ፕራግን 3 ለ 0 አሸንፏል። መሐመድ ኩዱስ፣ ዣቪ ሲመንስ እና የስላቪያ ፕራጉ ዴቫድ ዚማ በራሱ ላይ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጁል ኩንዴ ባስቆጠራቸው ግቦች ባርሴሎና ከመመራት ተነስቶ ኢንትራክት ፍራንክፈርትን 2 ለ 1 አሸንፏል። አንስጋር ናውፍ ለጀርመኑ ቡድን ብቸኛውን ጎል ከመረብ ጋር አገናኝቷል። በሌሎች ጨዋታዎች አትሌቲኮ ማድሪድ ፒኤስቪ አይንድሆቨንን እና ማርሴይ ዩኒየን ሴንት ጊሎይስን በተመሳሳይ 3 ለ 2 ሲያሸንፉ ሞናኮ ጋላታሳራይን 1 ለ 0 ረቷል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ባየር ሙኒክ ስፖርቲንግ ሊዝበንን 3 ለ 1፣ ኦሎምፒያኮስ ካይራት አልማቲን 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
ባየር ሙኒክ ስፖርቲንግ ሊዝበንን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Dec 10, 2025 55
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ የአውሮፓ ሊግ ሻምፒዮንስ ሊግ የስድስተኛ ጨዋታ መርሃ ግብር ዛሬ ማምሻውን ተጀምሯል። በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ባየር ሙኒክ ስፖርቲንግ ሊዝበንን 3 ለ 1 አሸንፏል። ሰርጌ ናብሪ፣ ሌናርት ካርል እና ጆናታን ታህ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የባየር ሙኒኩ ተከላካይ ጆሹዋ ኪሚች በራሱ ላይ ለስፖርቲንግ ግቧን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በውድድሩ አምስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ባየር ሙኒክ በ15 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ስፖርቲንግ ሊዝበን በ10 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሃ ግብር ኦሎምፒያኮስ ካይራት አልማቲን በጌልሰን ማርቲንስ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል።
የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናገደ
Dec 9, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ቦሌ ክፍለ ከተማ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳሳሽ ሰውአገኝ እና ሚሊዮን ጋይም የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዳግማዊት ሰለሞን ለኢትዮ ኤሌክትሪክ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ያለመሸነፍ ጉዞ 11ኛ ሳምንት ላይ ተገቷል። ቡድኑ 30 ነጥብ ላይ ረግቷል። በአንጻሩ በሊጉ አምስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ19 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ አጥቂ ዳግማዊት ሰለሞን በውድድር ዓመቱ ያስቆጠረቻቸውን ግቦች ወደ 17 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቷን አጠናክራለች። ዛሬ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድሬዳዋ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ12ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከታህሳስ 3 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እንደሚካሄዱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድሬዳዋ ከተማን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Dec 9, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድሬዳዋ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። ረፋድ ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ረድኤት አስረሳኸኝ በ43ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ቅድስት ዘለቀ የጨዋታ ኮከብ በመባል ተመርጣለች። በሊጉ ስምንተኛ ድሉን ያስመዘገበው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታዎች እየቀሩት በ25 ነጥብ ደረጃውን ከአራተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ12 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ በሊጉ ያስቆጠረቻቸውን ግቦች ወደ ዘጠኝ ከፍ በማድረግ ከኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን ቀጥላ በከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ‘ የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋል።
የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ጋር ይጫወታል
Dec 9, 2025 102
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ 7 ሰዓት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከቦሌ ክፍለ ከተማ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ ያደረጋቸውን 10 ጨዋታዎች አሸንፏል። 28 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያስቆጥር አምስት ግቦችን ተቆጥሮበታል። ቡድኑ በ30 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ተጋጣሚው ቦሌ ክፍለ ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው 10 ጨዋታዎች በአራቱ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይቷል። 11 ግቦችን ሲያስቆጥር 10 ጎሎችን አስተናግዷል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ16 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። ቦሌ ክፍለ ከተማ ካሸነፈ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። በሌላኛው መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከድሬዳዋ ከተማ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይጫወታሉ። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባከናወናቸው ስምንት ጨዋታዎች ሰባት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በስምንቱ ጨዋታዎች ላይ 26 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ የተቆጠረበት ጎል አንድ ብቻ ነው። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታዎች እየቀሩት በ22 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው 10 ጨዋታዎች አራቱን ሲያሸንፍ በስድስቱ ሽንፈትን አስተናግዷል። 10 ግቦችን ሲያስቆጥር 15 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ የሁለተኝነት ደረጃን ከሃዋሳ ከተማ ይረከባል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በ10ኛ ሳምንት በቦሌ ክፍለ ከተማ ካጋጠመው ሽንፈት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል።
በሻምፒዮንስ ሊግ ባየር ሙኒክ ከስፖርቲንግ ሊዝበን ኢንተር ሚላን ከሊቨርፑል የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Dec 9, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የስድስተኛ ጨዋታ መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል። ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ላይ ባየር ሙኒክ ከስፖርቲንግ ሊዝበን በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም ይጫወታሉ። ዘንድሮው በአውሮፓ መድረክ ጥሩ ግስጋሴ እያደረገ የሚገኘው ባየር ሙኒክ በ12 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ስፖርቲንግ ሊዝበን በ10 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ባየር ሙኒክ ካሸነፈ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ ያደርጋል። ኢንተር ሚላን ሊቨርፑልን ምሽት አምስት ላይ በጁሴፔ ሚኤዛ ስታዲየም የሚያስተናግድበት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የጣልያኑ ቡድን በ12 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ሊቨርፑል በዘጠኝ ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የሶስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ኢንተር ሚላን እና የስድስት ጊዜ የዋንጫው ባለቤት ሊቨርፑል የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌሎች መርሃ ግብሮች አትላንታ ከቼልሲ፣ ባርሴሎና ከኢንትራክት ፍራንክፈርት፣ ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከስላቪያ ፕራግ፣ ፒኤስቪ አይንድሆቨን ከአትሌቲኮ ማድሪድ፣ ሞናኮ ከጋላታሳራይ እና ዩኒየን ሴይንት ጊሎይስ ከማርሴይ በተመሳሳይ ከምሽቱ አምስት ላይ ይጫወታሉ። ካይራት አልማቲ ከኦሎምፒያክስ ከምሽቱ 12 ሰዓት ከ30 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ማንችስተር ዩናይትድ ዎልቭስን አሸነፈ
Dec 9, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 29/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 15ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር ማንችስተር ዩናይትድ ዎልቭስን 4 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በሞለኒው ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብሩኖ ፈርናንዴዝ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ብሪያን ምቡዌሞ እና ሜሰን ማውንት ቀሪዎቹን ጎሎችን ለዩናይትድ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጂን-ራይሰነር ቤልጋርድ ለዎልቭስ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ላይ ማንችስተር ዩናይትድ በዎልቭስ ላይ ከፍተኛ ብልጫ ወስዶ የተጫወተ ሲሆን ተጨማሪ ግቦችን ማስቆጠር የሚችልበትን እድል አልተጠቀመበትም። በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ዩናይትድ በ25 ነጥብ ደረጃውን ከ12ኛ ወደ 6ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ዎልቭስ በሁለት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። በከፍተኛ ውጤት ማጣት ቀውስ ውስጥ የሚገኘው ዎልቭስ በሊጉ ምንም ጨዋታ አላሸነፈም። በውጤቱ እጅጉን ደስተኛ ያልሆኑ አብዛኞቹ የዎልቭስ ደጋፊዎች ጨዋታው ከመጠናቀቁ በፊት ስታዲየሙን ለቀው ወጥተዋል። በ16ኛ ሳምንት ዎልቭስ ከሊጉ መሪ አርሰናል እና ማንችስተር ዩናይትድ ከቦርንማውዝ ይጫወታሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሲዳማ ቡና ልደታ ክፍለ ከተማን አሸነፈ
Dec 8, 2025 118
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 29/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና ልደታ ክፍለ ከተማን 3 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ምርጥነሽ ዮሐንስ፣ ኤልሳቤት ብርሃኑና ምትኬ ብርሃኑ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ፍቅርተ ካሳ ለልደታ ክፍለ ከተማ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። በሊጉ ሶስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ12 ነጥብ ደረጃውን ከ10ኛ ወደ 8ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ልደታ ክፍለ ከተማ በአምስት ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረጉ የ11ኛ ሳምንት ጨዋታዎች መቻል ባህር ዳር ከተማን 1 ለ 0 ሲያሸንፍ አዳማ ከተማ እና አዲስ አበባ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ መቻል ባህር ዳር ከተማን አሸነፈ
Dec 8, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 29/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቻል ባህር ዳር ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ እፀገነት ብዙነህ በ56ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ድሉን ያስመዘገበው መቻል በ23 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በሊጉ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ባህር ዳር ከተማ በአራት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል።
በፕሪሚየር ሊጉ ዎልቭስ ከማንችስተር ዩናይትድ ይጫወታሉ
Dec 8, 2025 98
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 29/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 15ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር በዎልቭስ እና ማንችስተር ዩናይትድ መካከል ዛሬ ይካሄዳል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ምሽት 5 ሰዓት ላይ በሞለኒው ስታዲየም ይደረጋል። ዎልቭስ በሁለት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ዩናይትድ በ22 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ21ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 20 ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ 10 ጊዜ ሲያሸንፍ ዎልቭስ 7 ጊዜ ድል ቀንቶታል። 3 ጊዜ አቻ ወጥቷል። በ20ዎቹ ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ 24 ግቦችን ሲያስቆጥር ዎልቭስ 22 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች በነበራቸው ግንኙነት ማንችስተር ዩናይትድ ሶስት ጊዜ፣ ዎልቭስ ደግሞ ሁለት ጊዜ ጨዋታዎችን አሸንፏል። መጥፎ የውድድር ዓመት እያሳለፈ የሚገኘው ዎልቭስ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ተጋጣሚው ማንችስተር ዩናይትድ በጥሩ አቋሙ ለመቀጠል ሶስት ነጥብ ያስፈልገዋል። የ40 ዓመቱ ማይክል ሳልስበሪ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ
Dec 8, 2025 83
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 29/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ የሁለተኛ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይደረጋሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከአዲስ አበባ ከተማ ይጫወታሉ። አዳማ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 10 ጨዋታዎች አራቱን ሲያሸንፍ አምስት ጊዜ ተሸንፏል። አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር 19 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ13 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ማሸነፍ የቻለው ጨዋታ አንድ ብቻ ነው። ስምንት ጊዜ ሲሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይቷል። አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 22 ግቦች ተቆጥረውበታል። በአራት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሃ ግብር መቻል ከባህር ዳር ከተማ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሊጉ ካከናወናቸው 10 ጨዋታዎች መካከል ስድስቱን ያሸነፈው መቻል ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 17 ግቦችን በ10ሩ ጨዋታዎች ላይ ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። መቻል በ20 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ባህር ዳር ከተማ በውድድር ዓመቱ 10 ጨዋታዎችን አድርጎ አንድ ጊዜ አሸንፎ በስምንቱ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 15 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ባህር ዳር ከተማ በአራት ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የዕለቱ የመጨረሻ መርሃ ግብር ልደታ ክፍለ ከተማ እና ሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ያገናኛል። ልደታ ክፍለ ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው 10 ጨዋታዎች ያሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በሰባቱ ሲሸነፍ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በ10ሩ ጨዋታዎች ላይ ሰባት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 19 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በሊጉ ካደረጋቸው ዘጠኝ ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን ሲያሸንፍ አራት ጊዜ ተሸንፏል። ሶስት ጊዜ ደግሞ አቻ መውጣት ችሏል። ስምንት ግቦችን ሲያስቆጥር 10 ጎሎችን አስተናግዷል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ሲዳማ ቡና በዘጠኝ ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል።
አርባምንጭ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና ነጥብ ተጋርተዋል
Dec 7, 2025 114
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 28/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዘጠነኛ ሳምንት ጨዋታ አርባምንጭ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተከናውኗል። ውጤቱን ተከትሎ አርባምንጭ ከተማ በአምስት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። አርባምንጭ በሊጉ ምንም ጨዋታ አላሸነፈም። ኢትዮጵያ ቡና በ11 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ጨዋታውን ተከትሎ የዘጠነኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። ፕሪሚየር ሊጉ በኢትዮጵያ ዋንጫ አራተኛ ዙር ጨዋታዎች ምክንያት የሚቋረጥ ሲሆን ውድድሩ ታህሳስ 10 ቀን 2018 ዓ.ም በ10ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ይመለሳል።
ፋሲል ከነማ እና መቀሌ 70 እንደርታ አቻ ተለያዩ
Dec 7, 2025 113
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 28/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዘጠነኛ ሳምንት ጨዋታ ፋሲል ከነማ እና መቀሌ 70 እንደርታ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ናትናኤል ማስረሻ በ89ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ግብ ፋሲል ከነማ መሪ ሆኗል። ፍጹም ዓለሙ በ92ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ግብ መቀሌ 70 እንደርታ በባከነ ሰዓት ወሳኝ አንድ ነጥብ እንዲያገኝ አስችሎታል። ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ፋሲል ከነማ ነጥቡን ወደ 17 ከፍ አድርጓል። ቡድኑ ከሊጉ መሪ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማጥበብ እድል አልተጠቀመበትም። መቀሌ 70 እንደርታ በአምስት ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። መቀሌ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ አላሸነፈም። በአሁኑ ሰዓት አርባምንጭ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል።
ነጌሌ አርሲ ድል ቀንቶታል
Dec 7, 2025 114
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 28/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዘጠነኛ ሳምንት ጨዋታ ነጌሌ አርሲ ሀዲያ ሆሳዕናን 2 ለ 1 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ከቤ ብዙነህ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥሯል። እዮብ አለማየሁ ለሀዲያ ሆሳዕና ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ ሶስተኛ ድሉን ያስመዘገበው አዲስ አዳጊው ነጌሌ አርሲ በ13 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሀዲያ ሆሳዕና በሰባት ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሸገር ከተማ አርባምንጭ ከተማን አሸነፈ
Dec 7, 2025 97
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 28/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሸገር ከተማ አርባምንጭ ከተማን 3 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሰርካለም ባሳ፣ ማርታ ወልዴ እና ህይወት ረጉ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሸገር ከተማ በሊጉ ሰባተኛ ድሉን በማስመዝገብ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ21 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ለሰባተኛ ጊዜ የተሸነፈው አርባምንጭ ከተማ በስምንት ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረገ የ11ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ ይርጋጨፌ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል።
ሃዋሳ ከተማ እና መቻል ነጥብ ተጋርተዋል
Dec 7, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 28/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዘጠነኛ ሳምንት ሃዋሳ ከተማ እና መቻል ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ጋናዊው ኮሊንስ ኮፊ በ38ኛው ደቂቃ ላይ በፍጹም ቅጣት ምት ባስቆጠራት ጎል መቻል መሪ ሆኗል። ጌታነህ ከበደ በ68ኛው ደቂቃ ሃዋሳ ከተማን አቻ ያደረገችውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ መቻል እና ሃዋሳ ከተማ በተመሳሳይ 14 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ስድስተኛ እና ሰባተኛ ደረጃን ይዘዋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሃዋሳ ከተማ ይርጋጨፌ ቡናን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Dec 7, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 28/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ ይርጋጨፌ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። ረፋድ ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ከአምላክነሽ ሃንቆ በ23ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። በሊጉ ስምንተኛ ድሉን ያስመዘገበው ሃዋሳ ከተማ በ25 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በ10 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል።