ቀጥታ፡
ስፖርት
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የከተማ ተራራ ላይ የብስክሌት ውድድርን በአፍሪካ ለመጀመሪያ ጊዜ ታስተናግዳለች
Apr 3, 2026 72
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 25/2018(ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፍ የከተማ ተራራ ላይ የብስክሌት ውድድር (City Mountain Bike Race) ሚያዚያ 25 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል። "ሲቲ ማውንቴን ባይክ ኤሊሚኔተር ፕሮ ሊግ" የሚል ስያሜ የተሰጠው ውድድር ዓለም አቀፉ የብስክሌት ህብረት (UCI) የውድድር መርሃ ግብር ውስጥ የተካተተና እውቅና ያለው ነው። ውድድሩ በአፍሪካ ሲካሄድ የኢትዮጵያው የመጀመሪያ መሆኑን የኢትዮጵያ ብስክሌት ፌዴሬሽን አስታውቋል። ውድድሩ ሚያዝያ 25 ቀን 2018 ዓ.ም በፒያሳ አድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም ዙሪያ ይካሄዳል። ውድድሩ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪዎች የሚሳተፉበት ዋናው ውድድር መሆኑን የኢትዮጵያ ብስክሌት ፌዴሬሽን አስታውቋል። በዓለም አቀፉ ውድድር ላይ ከ24 የአውሮፓ እና ከ10 የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ ከ60 እስከ 80 የሚደርሱ ምርጥ ብስክሌተኞች እንደሚሳተፉም ተገልጿል። ኢትዮጵያውያን የብስክሌት ስፖርተኞች በውድድሩ ተሳታፊ ናቸው። ይህም ኢትዮጵያን በዓመታዊው የዓለም አቀፍ የከተማ ማውንቴንባይክ ካሌንደር ውስጥ ከባርሴሎና በመቀጠል ሁለተኛዋ መዳረሻ ያደርጋታል። የኤሊት ተወዳዳሪዎች (ወንድ እና ሴት) የጊዜ ሙከራ፣ የግማሽ ፍጻሜ እና የፍጻሜ ውድድሮች ይከናወናሉ። ውድድሩ በዓለም አቀፉ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች በቀጥታ የሚተላለፍ ሲሆን፣ ከ20 ሚሊዮን በላይ ተመልካቾች ይከታተሉታል ተብሎ ይጠበቃል። ከዋናው ውድድር አስቀድሞ ሚያዚያ 24 ቀን 2018 ዓ.ም ለሁሉም ክፍት የሆነ ውድድር የሚካሄድ ሲሆን ኢትዮጵያውያን ብስክሌተኞች የመሳተፍ እድል ያገኛሉ። በዕለቱ የአማተር ብስክሌተኞች፣ የልጆች እና የሰዓት ሙከራ ውድድሮች ይካሄዳሉ። የኢትዮጵያ ብስክሌት ፌዴሬሽን ባወጣው መረጃ ዓለም አቀፍ ውድድሩን ለኢትዮጵያ ስፖርት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎች እንዳሉት ገልጿል። ውድድሩ ኢትዮጵያን ለዓለም ከማስተዋወቁ ባሻገር፣ ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና ያላቸውን ውድድሮች የማዘጋጀት አቅም እንዳላት በተግባር እንደሚያሳይ አመልክቷል። በተጨማሪም ኢትዮጵያውያን ተወዳዳሪዎች በሀገራቸው ከዓለም ኮከቦች ጋር የመወዳደር እድል እንዲያገኙና ወደ ዓለም አቀፍ የውድድር መድረክ እንዲሸጋገሩ ትልቅ ድልድይ እንደሚያገለግልም ነው ፌዴሬሽኑ ያስታወቀው። ለኢትዮጵያ የስፖርት ቱሪዝም እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ተብሎ ይታመናል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል 
Apr 3, 2026 115
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የማጣሪያ ጨዋታዎች በኋላ ዛሬ በ25ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ይመለሳል። ፕሪሚየር ሊጉ ላለፉት 18 ቀናት ተቋርጦ ነበር። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከባህር ዳር ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ ካደረጋቸው 24 ጨዋታዎች መካከል ዘጠኝ ጊዜ ሲያሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በ10 ጨዋታዎች ላይ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ 13 ግቦችን ሲያስቆጥር 13 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ37 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ባህር ዳር ከተማ በውድድር ዓመቱ 24 ጨዋታዎችን አከናውኖ በስድስቱ ድል ሲቀናው አምስት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ 13 ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 17 ግቦችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ 17 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ባህር ዳር ከተማ በ31 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ካሸነፈ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። ደረጃውንም ወደ ሶስተኛ ከፍ ያደርጋል። ባህር ዳር ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። በሌላኛው መርሐ- ግብር መቻል ከምድረ ገነት ሽሬ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቻል እስከ አሁን በሊጉ 24 ጨዋታዎችን ያደረገ ሲሆን ዘጠኝ ጨዋታዎችን ሲያሸንፍ ስድስት ጊዜ ተሸንፏል። በዘጠኝ ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ24ቱ ጨዋታዎች ላይ 29 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 19 ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ36 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ምድረ ገነት ሽሬ በበኩሉ ካከናወናቸው 24 ጨዋታዎች መካከል ስድስት ጊዜ ድል ሲቀናው በዘጠኙ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ዘጠኝ ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 16 ግቦችን ሲያስቆጥር 19 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ምድረ ገነት ሽሬ በ27 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው መቻል ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። ምድረ ገነት ሽሬ ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ድሬዳዋ ከተማ ከፋሲል ከነማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ድሬዳዋ ከተማ በ28 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ፋሲል ከነማ በ35 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት የሊጉ ጨዋታዎች የተሸነፈው ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ፋሲል ከነማ ባለፉት ሰባት ጨዋታዎች ከድል የራቀ ሲሆን ማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ እንዲያገኝ ያስችለዋል። ከቀኑ 10 ሰዓት ሸገር ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በ30 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ19 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሸገር ከተማ ካሸነፈ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። አርባምንጭ ከተማ ድል ከቀናው በሊጉ አራተኛ ድሉን ያገኛል። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት እስከ መጋቢት 27 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ሲዳማ ቡና በ45 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ አዲስ ግደይ በተመሳሳይ 10 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በጋራ እየመሩ ነው። የፋሲል ከነማው ታምራት እያሱ በስምንት ግቦች ይከተላል።
ኢትዮጵያ በፊፋ የዓለም አገራት ወርሃዊ ደረጃ ደረጃዋን አሻሻለች
Apr 2, 2026 113
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018 (ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) በየወሩ ይፋ በሚያደርገው የአገራት እግር ኳስ ደረጃ ኢትዮጵያ ሶስት ደረጃዎችን አሻሽላለች። ፊፋ የእ.አ.አ ማርች ወር 2025 የሀገራት ወርሃዊ የእግር ኳስ ደረጃን ይፋ አድርጓል። በዚሁ መሰረት ኢትዮጵያ ከነበረችበት 147ኛ ደረጃ ወደ 144ኛ ከፍ ብላለች። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔን በድምር ውጤት 4 ለ 0 በማሸነፍ ወደ ምድብ ማጣሪያው ማለፉ ለደረጃው መሻሻል አስተዋጽኦ አድርጓል።   ሞሮኮ ከዓለም ስምንተኛ ከአፍሪካ አንደኛ ደረጃን ይዛለች። ሴኔጋል 14ኛ፣ ናይጄሪያ 26ኛ፣ አልጄሪያ 28ኛ፣ ግብጽ 29ኛ፣ ኮትዲቯር 34ኛ፣ ቱኒዚያ 44ኛ እና ካሜሮን 45ኛ የተሻለ ደረጃ ያላቸው የአፍሪካ ሀገራት ናቸው። ለ23ኛው የዓለም ዋንጫ ያለፈችው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ደረጃውን ከ48ኛ ወደ 46ኛ ከፍ አድርጋለች። ፈረንሳይ በፊፋ ወርሃዊ የሀገራተ ደረጃ የመጀመሪያውን ደረጃ ይዛለች። ስፔን ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። የወቅቱ የዓለም ዋንጫ አሸናፊ አርጀንቲና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። እንግሊዝ፣ ፖርቹጋል፣ ብራዚል እና ኔዘርላንድስ ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ደረጃን ይዘዋል። ከ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ውጪ የሆነችው ጣልያን 12ኛ ደረጃን ይዛለች። የአውሮፓዋ ሳን ማሪኖ የመጨረሻው 211ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። የቡድን ጥንካሬ፣ የሚደረገው ጨዋታ ያለው ወሳኝነት፣ የጨዋታ ውጤትና ከጨዋታ በፊት የሚጠበቅ ውጤት ፊፋ የሀገራትን የእግር ኳስ ደረጃ የሚለካባቸው መመዘኛዎች ናቸው።
የባህል ስፖርቶች ውድድርና ፌስቲቫል አብሮነት እንዲጠናከር እያገዘ ነው
Apr 2, 2026 107
ሐረር ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦ የባህል ስፖርቶች ውድድርና ፌስቲቫል መካሔዱ ክልሎች ያላቸውን ባሕልና እሴት ለማስተዋወቅና አብሮነትን ለማጠናከር ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ ተገለጸ። 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድርና 19ኛው የባህል ስፖርት ፌስቲቫል "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ በሐረሪ ክልል እየተካሄደ ይገኛል።   በውድድሩና ፌስቲቫሉ በ11 የስፖርት ዓይነቶች ከ1ሺህ 500 በላይ ስፖርተኞች እየተሳተፉ ይገኛሉ ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ተሳታፊዎች የባህል ስፖርቶች ውድድርና ፌስቲቫሉ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች የእርስ በእርስ ትውውቅን ለማሳደግና የባህል ግንኙነትን ለማጠናከር የሚያግዝ ነው ብለዋል። ከተሳታፊዎቹ መካከል ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመጣው ፍጹም ገላና የባህል ውድድሩና ፌስቲቫሉ የብሔር ብሔረሰቦችን ባህልና ትውፊት እንድናውቅ ረድቶናል ሲል አመልክቷል።   በተለይም የብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች አንድነት ይበልጥ እንዲጎለብት ያደርጋል ብሏል። ውድድሩና ፌስቲቫሉ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች አኩሪ ባህሎቻቸውን ለማስተዋወቅ ምቹ ዕድል ፈጥሯል ያለችው ደግሞ ከአማራ ክልል የባህል ስፖርት ተሳታፊዋ ስንዱ መላዕክ ናት።   በፌስቲቫሉ የእርስ በርስ የባህል ልውውጥ እያደረጉ እንደሚገኙና ይህም አብሮነትን ከማጠናከሩ ባለፈ ለሰላም ግንባታ የጎላ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ነው የምትናገረው። ከኦሮሚያ ክልል ውድድሩና ፌስቲቫሉ ላይ ለመሳተፍ የመጣው ወጣት በላይ ደረሱ "ፌስቲቫሎችና ውድድሮቹ የማናውቃቸውን ባህላዊ ጨዋታዎች፣ እሴቶች፣ ባህልና ወጎችን ለማወቅ አስችሎናል" ነው ያለው።   የባህል ውድድሩና ፌስቲቫሉ የጋራ እሴቶችን አጉልቶ ለማውጣት፣ ወንድማማችነትን ለማጠናከርና አንዱ የሌላውን ባህል ለማወቅ ፋይዳው የጎላ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የሲዳማ ክልል የልዑካን ቡድን አባል አቶ ማዕረግ በቀለ ናቸው።   ይህም በህዝቦች መካከል ሰላም፣ አንድነትና መከባበርን በማጎልበት ረገድ ሚናው የላቀ መሆኑን አመላክተዋል። 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድርና 19ኛው የባህል ስፖርት ፌስቲቫል የፊታችን እሁድ ፍጻሜውን ያገኛል።
ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከ52 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ አለፈች
Apr 1, 2026 131
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የክፍለ አህጉራት የመጨረሻ ማጣሪያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ጃማይካን 1 ለ 0 አሸንፋለች።   ከእኩለ ሌሊት በኋላ በሜክሲኮ አክሮን ስታዲየም የተካሄደው ጨዋታ መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ግብ አቻ በመጠናቀቁ ወደ ጭማሪ ሰዓት አምርቷል። በጭማሪ ሰዓት የተከላካይ መስመር ተጫዋቹ አክሴል ቱዋንዜቤ በ100ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። የጨዋታው ኮከብም ሆኗ ተመርጧል። በጨዋታው የማዕከላዊ አፍሪካዊቷ ሀገር የተሻለ ብልጫ በመውሰድ ተጫውታለች።   ውጤቱን ተከትሎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከ52 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫ በማለፍ ታሪክ ሰርታለች። የማዕከላዊ አፍሪካዊቷ ሀገር ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ1974 በጀርመን (በወቅቱ አጠራሯ ምዕራብ ጀርመን) አስተናጋጅነት በተካሄደው 10ኛው የዓለም ዋንጫ ነው። አሁን ለሁለተኛ ጊዜ በውድድሩ ላይ ትከፈላለች። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የምትሳተፍ 10ኛ የአፍሪካ ሀገርም ሆናለች። ሞሮኮ፣ ሴኔጋል፣ ግብጽ፣ ኮትዲቯር፣ አልጄሪያ፣ ቱኒዚያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ጋና እና ኬፕ ቨርዴ ለዓለም ዋንጫ ያለፉ የአፍሪካ ሀገራት ናቸው። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በዓለም ዋንጫው በምድብ 11 ከፖርቹጋል፣ ኡዝቤኪስታን እና ኮሎምቢያ ጋር ጨዋታዎቿን ታደርጋለች። አፍሪካ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ 10 ሀገራት በዓለም ዋንጫው ታሳትፋለች። ጃማይካ ከ28 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫው የመመለስ ውጥኗ አልተሳካም።
ጣልያን ከዓለም ዋንጫ ውጭ ሆነች
Apr 1, 2026 98
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ዞን የፍጻሜ ማጣሪያ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። ትናንት ማምሻውን በቢሊኖ ፖልጄ ስታዲየም በተካሄደውጨዋታ ቦስኒያ እና ሄርዞጎቪና ጣልያንን 4 ለ 1 በመለያ ምት አሸንፋለች። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሃሪስ ታባኮቪች ለቦሲኒያ፣ ሞይስ ኪን ለጣልያን ግቦቹን አስቆጥረዋል። የጣልያኑ አሌሳንድሮ ባስቶኒ በ41ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በጭማሪ 30 ደቂቃ ተጨማሪ ጎል ባለመቆጠሩ አሸናፊውን በመለያ ምት መለየት ግድ ሆኗል። በዚህ ቦሲኒያ 4 ለ 1 በማሸነፍ ከ12 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫው ማለፏን አረጋግጣለች። ሶስት ሚሊዮን ህዝብ ያላት ቦሲኒያ ለሁለተኛ ጊዜ በዓለም ዋንጫው ትሳተፋለች። ጣልያን ከ20ኛው የዓለም ዋንጫ በኋላ ዓለም ትልቁ የእግር ኳስ መድረክ የመመለስ ህልሟ አልተሳካም። አዙሪዎቹ ለሶስት ተከታታይ የዓለም ዋንጫ ማለፍ አልቻሉም።   በሌላኛው ጨዋታ ስዊድን ፖላንድን 3 ለ 2 አሸንፋለች። በስትሮውበሪ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶኒ ኢላንጋ፣ ጉስታፍ ላገርቢልክ እና ቪክቶር ዮኮሬሽ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የአርሰናሉ አጥቂ ዮኮሬሽ በ88ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ ስዊድንን ለዓለም ዋንጫ አሳልፏታል። ኒኮላ ዛሌውስኪ እና ካሮል ስዊዴርስኪ ለፖላንድ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።   በፋዲል ቮክሪ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቱርክዬ ኮሶቮን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ኬረም አክቱርኮግሉ ግቧን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ቼክ ሪፐብሊክ ዴንማርክን በመለያ ምት 3 ለ 1 አሸንፋለች። ሁለቱ ቡድኖች በ12ዐ ደቂቃ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። በኢፒኢቲ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፓቬል ሱልች እና ላዲስላቭ ክሬጄቺ ለቼክ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዮአኪም አንደርሰን እና ካስፐር ዋርትስ ሆግ ለዴንማርክ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጨዋታው በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ በመጠናቀቁ ምክንያት ወደ ጭማሪ ሰዓት አምርቷል። ላዲስላቭ ክሬጄቺ ለቼክ፣ ዋርትስ ሆግ በጭማሪ ሰዓት ግብ አስቆጥረዋል። ቡድኖቹ ወደ መለያ ምት አምርተው ቼክ ሪፐብሊክ 3 ለ 1 በማሸነፍ ለዓለም ዋንጫ አልፋለች። ውጤቱን ተከትሎ ስዊድን፣ቱርክዬ፣ቼክ ሪፐብሊክ እና ቦሲኒያና ሄርዞጎቪና ለ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ አልፈዋል። አራቱ ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራት ተቀላቅለዋል። አውሮፓ በዓለም ዋንጫው 16 ሀገራትን ታሳትፋለች።
ኢራቅ ከ40 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫ ተመልሳለች
Apr 1, 2026 93
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የክፍለ አህጉራት የፍጻሜ ማጣሪያ ኢራቅ ቦሊቪያን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ዛሬ ማለዳ ላይ በሜክሲኮ በቢቢቪኤ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አሊ አል ሃማዲ እና አይማን ሁሴን የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሞሰስ ፓኒያጉዋ ለቦሊቪያ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ቦሊቪያ የተሻለ ብልጫ የነበራት ቢሆንም ኢራቅ ከፈጠረቻቸው ሶስት ኢላማቸውን የጠበቁ ሙከራዎች መካከል ሁለቱን ወደ ግብ በመቀየር ውጤታማ ሆናለች። ግብ ያስቆጠረው የኢራቁ አይማን ሁሴን የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጧል። ኢራቅ ከ40 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ አልፋለች። የሜሶፖታሚያ አንበሶች ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፉት እ.አ.አ በ1986 ሜክሲኮ ባዘጋጀችው 11ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ነበር። ኢራቅ በውድድሩ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ ትሳተፋለች። ቦሊቪያ ከ32 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ የማለፍ ህልሟ አልተሳካም። ለመጨረሻ በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ1994 በአሜሪካ በተዘጋጀው 15ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ላይ ነው። ትናንት ከእኩለ ሌሊት በኋላ በሜክሲኮ አክሮን ስታዲየም በተካሄደው የክፍለ አህጉራት የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ጃማይካን 1 ለ 0 በማሸነፍ ከ52 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ትልቁ የእግር ኳስ መድረክ ተመልሳለች። በአውሮፓ ትናንት ማምሻውን የተካሄዱ የጥሎ ማለፍ ማጣሪያ ጨዋታዎችን ተከትሎ ስዊድን፣ ቱርኪዬ፣ ቼክ ሪፐብሊክ እና ቦሲኒያና ሄርዞጎቪና ለዓለም ዋንጫ አልፈዋል። ጣልያን በመለያ ምት ተሸንፋ ከ12 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫ የመመለስ ህልሟ ተጨናግፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ ለዓለም ዋንጫ ያለፉ ሀገራት ሙሉ ለሙሉ ተለይተዋል።   23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ከሰኔ 4 እስከ ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም በአሜሪካ፣ ሜክሲኮ እና ካናዳ ጣምራ አዘጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ 48 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ሮቤርቶ ዴ ዘርቢ የቶተንሃም ሆትስፐርስ አሰልጣኝ ሆነው ተሾሙ 
Mar 31, 2026 174
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ ቶተንሃም ሆትስፐር ጣልያናዊውን አሰልጣኝ ሮቤርቶ ዴ ዘርቢን በአምስት ዓመት ኮንትራት አዲሱ ዋና አሰልጣኝ አድርጎ መሾሙን ዛሬ ይፋ አድርጓል። ክለቡ ይህንን ውሳኔ ያሳለፈው የቀድሞው ጊዜያዊ አሰልጣኝ ኢጎር ቱዶር በቆይታቸው ደካማ ውጤት በማስመዝገባቸውና ክለቡን ለወራጅ ቀጠና ስጋት ይበልጥ ማጋለጣቸውን ተከትሎ መሆኑን ስካይ ስፖርትስ ዘግቧል። የ46 ዓመቱ አሰልጣኝ ዴ ዘርቢ ከክለቡ አመራሮች ጋር ባደረጉት ስምምነት መሰረት እስከ 2031 ድረስ በለንደኑ ክለብ ለመቆየት ፊርማቸውን አኑረዋል። ዴ ዘርቢ ክለቡን በአሰልጣኝነት የተረከቡት ከፈርንሳዩ ማርሴይ ጋር በጋራ ስምምነት መለያየታቸውን ተከትሎ ነው። በውላቸው ላይ ክለቡ ወደ ታችኛው ሊግ ቢወርድ እንኳ ኮንትራቱን የሚያቋርጥ አንቀጽ (relegation clause) አለማካተቱ፣ በአሰልጣኙ ላይ ያለውን የረጅም ጊዜ እምነት እንደሚያሳይ ተገልጿል። ዴ ዘርቢ የክለቡ አሰልጣኝ ከሆኑ በኋላ በሰጡት መግለጫ ቶተንሃምን የመሰለ ታላቅ ክለብ በመቀላቀላቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። የክለቡ አመራሮች ያላቸው የወደፊት ራዕይ እና የሚከተሉት የማጥቃት እግር ኳስ ፍልስፍና ወደ ክለቡ እንዲመጡ እንዳነሳሳቸው ተናግረዋል። አሰልጣኙ ደጋፊዎችን የሚያስደስት ጨዋታ ለማሳየት ቃል ገብተዋል። የአሰልጣኙ አፋጣኝ እና ቀዳሚ ተግባር ቶተንሃም በዘንድሮው የውድድር ዘመን በፕሪምየር ሊጉ እንዲቆይ ማድረግ ነው። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ30 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። 18ኛ ደረጃ ላይ ከሚገኘው ዌስትሃም ዩናይትድ የሚበልጠው በአንድ ነጥብ ነው። ክለቡ ባለፉት 13 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ቀሪዎቹ ሰባት ጨዋታዎች ለአሰልጣኙ ትልቅ ፈተና እንደሚሆኑ ይጠበቃል። ሮቤርቶ ዴ ዘርቢ የመጀመሪያ የሊግ ጨዋታቸውን የሚያደርጉት ሚያዝያ 4 ቀን 2018 ዓ.ም ከሰንደርላንድ ጋር በ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ነው። እስከ ውድድር ዘመኑ ፍጻሜ ድረስ ክለቡን በደረጃ ሰንጠረዡ ከፍ ለማድረግ በሙሉ ትኩረት እና ትጋት እንደሚሰሩ አሰልጣኝ ዴ ዘርቢ አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ ወደ ምድብ ማጣሪያው አለፈች
Mar 31, 2026 184
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ኢትዮጵያ ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔን 1 ለ 0 አሸንፋለች። በድሬዳዋ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቸርነት ጉግሳ በሰባተኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ዋልያዎቹ በጨዋታው ላይ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድሎችን በመፍጠር የተሻሉ ነበሩ። ከእረፍት መልስ ቸርነት ጉግሳ ያልተጠቀመባት ግልጽ የግብ እድል በጨዋታው ተጠቃሽ ከሚባሉ ክስተቶች መካከል አንዱ ነው። በርካታ ደጋፊዎች በድሬዳዋ ስታዲየም በመገኘት ጨዋታውን ተከታትለውታል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ በድምር ውጤት በማሸነፍ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ወደ ምድብ ድልድል ማለፏን አረጋግጣለች። ብሔራዊ ቡድኑ በመጀመሪያው ጨዋታ 3 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣሪያ ከመስከረም እስከ ህዳር ወር 2019 ዓ.ም ይካሄዳል። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ በ2027 በታንዛንያ፣ ኬንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታዋን ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ታደርጋለች 
Mar 31, 2026 139
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታዋን ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ዛሬ ያከናውናል። የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታ በድሬዳዋ ስታዲየም ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ይካሄዳል። ሀገራቱ መጋቢት 18 ቀን 2018 ዓ.ም በሞሮኮ ኤል አብዲ ስታዲየም ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ 3 ለ 0 ማሸነፏ ይታወቃል። አቤል ያለው ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ከነዓን ማርክነህ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ በአሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ የሚመሩት ዋልያዎቹ ወደ ምድብ ድልድል የመግባት እድላቸውን አስፍተዋል። ብሔራዊ ቡድኑ ለመልሱ ጨዋታ ዝግጅት መጋቢት 20 ቀን 2018 ዓ.ም ድሬዳዋ የደረሰ ሲሆን የመጨረሻ ልምምዱን ጨዋታው በሚካሄድበት ድሬዳዋ ስታዲየም ትናንት ማምሻውን አድርጓል። አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ከጨዋታው በፊት ትናንት በሰጡት መግለጫ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ላይ ባገኘው ድል ሳይዘነጋ የመልሱን ጨዋታ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንደሚገባ ገልጸዋል። አሰልጣኙ ቢኒያም አይተን በጉዳት ምክንያት ከነገው ጨዋታ ውጪ መሆኑን ጠቁመዋል። ከቢኒያም ውጪ ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ በጤንነት ላይ መሆናቸውን አንስተዋል። በአባቱ ድንገተኛ ህልፈት ምክንያት በመጀመሪያው ጨዋታ ያልነበረው የቡድኑ አምበል ጋቶች ፓኖም ለመልሱ ጨዋታ ከብሔራዊ ቡድኑ ጋር በመቀላቀል ልምምድ ማድረጉን አመልክተዋል። በ47 ዓመቱ ፓርቹጋላዊ ሪካርዶ ሞናሳንቶ የሚመራው የሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ብሔራዊ ቡድን ጨዋታውን ለማድረግ ከትናንት በስቲያ ድሬዳዋ መግባቱ ይታወቃል። የመጨረሻ ልምምዱንም ትናንት በድሬዳዋ ስታዲየም ሰርቷል። ካፍ የነገው የኢትዮጵያ እና ሳኦቶሜ ጨዋታ በዝግ እንዲካሄድ ውሳኔ አሳልፎ ነበር። የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በስታዲየሙ ዙሪያ የተሰጡ የግምገማ አስተያየቶችን መሰረት በማድረግ በፍጥነት ለማስተካከል እርምጃ ወስዷል። የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ከከተማ አስተዳደሩ እርምጃ ጎን ለጎን ጨዋታው ለተመልካች ክፍት እንዲሆን ባደረገው ከፍተኛ ጥረት እንዲሁም የካፍ ሴኪዩሪቲ ኦፊሰር በአካል ተገኝተው ከገመገሙ በኋላ በላኩት ሪፖርት መሰረት ካፍ 10 ሺህ ተመልካች በስታዲየም ተገኝቶ እንዲከታተል ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቋል። ኢትዮጵያ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈች ወደ ምድብ ድልድል ምዕራፍ ማለፏን ታረጋግጣለች።
ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከ52 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ ታልፍ ይሆን?   
Mar 31, 2026 137
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018(ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የሚሳተፉ ቀሪ ሀገራት የሚለዩባቸው የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች የተመልካቾችን ትኩረት ስበዋል። በዓለም ዋንጫው የክፍለ አህጉራት የፍጻሜ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። አፍሪካዊቷ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከጃማይካ ጋር ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት በሜክሲኮ አክሮን ስታዲየም ይጫወታሉ። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ (48ኛ) በመያዟ ቀጥታ ለዛሬው የፍጻሜ ጨዋታ አልፋለች። ጃማይካ በግማሽ ፍጻሜው ኒው ካሌዶኒያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። የማዕከላዊ አፍሪካዊቷ ሀገር ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ1974 በጀርመን (በወቅቱ አጠራሯ ምዕራብ ጀርመን) አስተናጋጅነት በተካሄደው 10ኛው የዓለም ዋንጫ ነው። ውድድሩ የሀገሪቷ ብቸኛ የዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ነው። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ካሸነፈች ከ52 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫ በማለፍ ታሪክ የመስራት እድል ታገኛለች። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የምትሳተፍ 10ኛ የአፍሪካ ሀገር ትሆናለች። ሞሮኮ፣ ሴኔጋል፣ ግብጽ፣ ኮትዲቯር፣ አልጄሪያ፣ ቱኒዚያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ጋና እና ኬፕ ቨርዴ ለዓለም ዋንጫ ያለፉ የአፍሪካ ሀገራት ናቸው። በሌላኛው መርሐ ግብር ቦሊቪያ ከኢራቅ ነገ ማለዳ 12 ሰዓት ላይ በቢቢቪኤ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢራቅ ኮንጎ በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ (55ኛ) በመያዟ ለጥሎ ማለፍ የፍጻሜ ጨዋታው በቀጥታ አልፋለች። ቦሊቪያ በግማሽ ፍጻሜ ማጣሪያው ሱሪናምን 2 ለ 1 በማሸነፍ ለወሳኙ ጨዋታ ደርሳለች። አሸናፊ ሀገራት ለዓለም ዋንጫው ያልፋሉ። በተያያዘም የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ዞን የጥሎ ማለፍ የፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ። ቦሲኒያ እና ሄርዞጎቪና ከጣልያን ጋር ምሽት 3 ሰዓት ከ45 ላይ በቢሊኖ ፖልጄ ስታዲየም ይጫወታሉ። የአራት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ጣልያን ከ12 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫው ለመመለስ የምታደርገው ጨዋታ ትኩረት ስቧል። አዙሪዎቹ ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፉት እ.አ.አ በ2014 ብራዚል ባዘጋጀችው 20ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ነው። ጣልያን ባለፉት ሁለት የዓለም ዋንጫዎች አለመሳተፏ በዓለም እግር ኳስ ውስጥ ትልቅ መነጋገሪያ የሆነ ጉዳይ ነው። በ48 ዓመቱ ጄናሮ ጋቱሱ የሚመራው የጣልያን ብሔራዊ ቡድን ወደ ዓለም ዋንጫው የሚያሳልፋትን ትኬት ለመቁረጥ ቦስኒያን መርታት ይጠበቅበታል። በሌሎች መርሐ ግብሮች ስዊድን ከፖላንድ፣ ቼክ ሪፐብሊክ ከዴንማርክ እና ኮሶቮ ከቱርኪዬ በተመሳሳይ ምሽት 3 ሰዓት ከ45 ላይ ይጫወታሉ። በጥሎ ማለፉ የሚያሸንፉ አራት ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ። አውሮፓ በ23ኛው የዓለም ዋንጫ 16 ሀገራትን ተሳትፋለች።
ካፍ የኢትዮጵያ እና የሳኦቶሜና ፕሪንሲፔ ጨዋታን 10 ሺህ ተመልካች ስታዲየም ተገኝቶ እንዲከታተለው ወሰነ
Mar 30, 2026 207
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከሳኦቶሜና ፕሪንሲፔ አቻው ጋር የሚያደርገውን የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ 10 ሺህ ተመልካች በድሬዳዋ ስታዲየም ተገኘቶ እንዲከታተለው መወሰኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታወቀ። ካፍ የነገው የኢትዮጵያ እና ሳኦቶሜ ጨዋታ በዝግ እንዲካሄድ ውሳኔ አሳልፎ ነበር። የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በስታዲየሙ ዙሪያ የተሰጡ የግምገማ አስተያየቶችን መሰረት በማድረግ በፍጥነት ለማስተካከል እርምጃ መውሰዱን ፌዴሬሽኑ አመልክቷል። የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ከከተማ አስተዳደሩ እርምጃ ጎን ለጎን ጨዋታው ለተመልካች ክፍት እንዲሆን ባደረገው ከፍተኛ ጥረት እንዲሁም የካፍ ሴኪዩሪቲ ኦፊሰር በአካል ተገኝተው ከገመገሙ በኋላ በላኩት ሪፖርት መሰረት ካፍ 10 ሺህ ተመልካች በስታዲየም ተገኝቶ እንዲከታተል ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቋል። የሁለቱ ቡድኖች የመልስ ጨዋታ ነገ ከቀኑ 10 ሰዓት በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል።
ባስመዘገብነው የመጀመሪያ ድል ሳንዘናጋ የመልሱን ጨዋታ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንገባለን - አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ  
Mar 30, 2026 193
ድሬዳዋ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ላይ ባገኘው ድል ሳይዘነጋ የመልሱን ጨዋታ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንደሚገባ የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ተናገሩ። አሰልጣኝ ዮሐንስ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ የሚደረገውን የመልስ ጨዋታ አስመልክቶ ዛሬ በድሬዳዋ ስታዲየም ለመገናኛ ብዙሃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። አሰልጣኙ በመግለጫቸው ዋልያዎቹ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታን ለማሸነፍ የሚያስችላቸውን ዝግጅት አድርገዋል ሲሉ ገልጸዋል። ዋልያዎቹ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ሞሮኮ ላይ ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ 3 ለ 0 ማሸነፋቸውን አስታውሰው፤ ይህ ውጤት በምንም መንገድ መዘናጋት ሳይፈጥር ነገ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንገባለን ብለዋል። የብሔራዊ ቡድኑ ተጫዋቾች በጥሩ የማሸነፍ መንፈስ ታጅበው እንደሚጫወቱ ተናግረዋል። ተጫዋቾቹ በቂ ልምምድ ማካሄዳቸውንና በስነ-ልቦናም ጭምር ማሸነፍ የሚያስችላቸውን ዝግጅት ማድረጋቸውንም ነው የገለጹት። በአባቱ ድንገተኛ ህልፈት ምክንያት በመጀመሪያው ጨዋታ ያልነበረው የቡድኑ አምበል ጋቶች ፓኖም ለመልሱ ጨዋታ ከብሔራዊ ቡድኑ ጋር በመቀላቀል ልምምድ ማድረጉን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ነገ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር የሚካሄደውን የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ካሸነፈ ወደ ምድብ ድልድሉ ይቀላቀላል። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምስራቅ አፍሪካ አገራት በሆኑት ኬንያ፣ ታንዛኒያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት እ.አ.አ ጁን 2027 ይካሄዳል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የ55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና አጠቃላይ አሸናፊ ሆነ
Mar 29, 2026 323
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ ከመጋቢት 15 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በአደይ አበባ ዓለም አቀፍ ስታዲየም ሲካሄድ የቆየው 55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ተጠናቋል። በሻምፒዮናው ላይ 36 ክለቦች፣ ተቋማት፣ 9 ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተሳተፉ ሲሆን፤ 621 ወንድ፣ 436 ሴት በድምሩ 1057 ተወዳዳሪዎች ተሳትፈዋል።   ሻምፒዮናው ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት፣ ለአትሌቶች የውድድር እድል ለመፍጠር ፣ አትሌቶችን በሽልማት የማበረታታት ዓላማ ያለው ነው። በውድድሩ ማብቂያ ቀን 10 የፍጻሜ ውድድሮች ተካሄደዋል።   ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሻምፒዮናው አጠቃላይ አሸናፊ በመሆን አጠናቋል። መቻል ሁለተኛ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሶስተኛ ደረጃን ይዘው መጨረሳቸውን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በሻምፒዮናው መዝጊያ ላይ የተገኙት የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ኮማንደር ስለሺ ስህን እና ሌሎች የፌዴሬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች ለክለቦች እና አትሌቶች የተዘጋጁ የገንዘብ፣ የዋንጫና ሜዳሊያ ሽልማቶችን አበርክተዋል። ፌዴሬሽኑ ለውድድሩ ለማካሄድ 10 ሚሊዮን ብር ወጪ ማድረጉን አስታውቋል።   ዘመናዊ የሰዓት መመዝገቢያ ማሽን (Time Tronics) በሻምፒዮናው ላይ ተግባራዊ ሆኗል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ፌዴሬሽኑ በየዓመቱ ከሚያካሂዳቸው ውድድሮች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው።
ዋልያዎቹ ከሞሮኮ መልስ የመጀመሪያ ልምምዳቸውን አድርገዋል
Mar 29, 2026 232
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ለሚያደርገው የመልስ ጨዋታ የመጀመሪያ ልምምዱን ማምሻውን በድሬዳዋ ስታዲየም ሰርቷል።   በአባቱ ድንገተኛ ህልፈተ ሕይወት ምክንያት በመጀመሪያው ጨዋታ ያልነበረው የብሔራዊ ቡድኑ አምበል ጋቶቾ ፓኖም ስብስቡን ተቀላቅሎ ልምምድ አድርጓል። የዋልያዎቹ ተጋጣሚ የሆኑት ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ዛሬ ከቀትር በኋላ ድሬዳዋ መግባታቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።   የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች የመልስ ጨዋታ ማክሰኞ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ ከትናንት በስቲያ ሞሮኮ ላይ በተካሄደው የመጀመሪያ ጨዋታ 3 ለ 0 አሸንፋለች።   በአሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ የሚመራው ብሔራዊ ቡድን በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ ወደ ምድብ ድልድል መግባቱን ያረጋግጣል።   36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ በ2027 በታንዛንያ፣ ኬንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት ይካሄዳል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም