ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ኢትዮጵያ ወሳኝ ድል ተቀዳጀች
Mar 27, 2026 67
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፦ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በሞሮኮ ኤል አብዲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አቤል ያለው ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ከነዓን ማርክነህ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ዋልያዎቹ ብልጫ ወስደው ተጫውተዋል። የማጥቃት እንቅስቃሴያቸው ጥሩ የሚባል ነበር። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ድልድል የመግባት እድሏን አስፍታለች። የሁለቱ ሀገራት የመልስ ጨዋታ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ ወደ ምድብ ድልድል ማለፉን ያረጋግጣል። የብሔራዊ ቡድኑ ዋና አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ በመጀመሪያ ጨዋታቸው ድል ቀንቷቸዋል። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ ጁን 2027 በታንዛንያ፣ ኬንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት ይካሄዳል።
ጣልያን ዴንማርክ እና ስዊድን ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ የጥሎ ማለፍ ፍጻሜ አለፉ
Mar 27, 2026 73
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ዞን የመጀመሪያ ዙር የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። በቤርጋሞ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጣልያን ሰሜን አየርላንድን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ሳንድሮ ቶናሊ እና ሞይስ ኪን ጎሎቹን አስቆጥረዋል። በሌላኛው መርሐ ግብር ዴንማርክ ሰሜን ሜቄዶናያን 4 ለ 0 ረታለች። በፓርከን ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ጉስታቭ ኢሳክሰን ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሚኬል ዳምስጋርድ እና ክርስቲያን ኖርጋርድ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ስዊድን ዩክሬንን 3 ለ 1 አሸንፋለች። በቫሌንሺያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአርሰናሉ አጥቂ ቪክቶር ዮኮሬሽ ሁለት ግቦችን በጨዋታ ቀሪውን ጎል በጨዋታ በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ማትቪይ ፖኖማሬንኮ ለዩክሬን ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ፖላንድ በሮበርት ሎዋንዶውስኪ እና ፒተር ዚሊኒሲኪ ጎሎች አልባኒያን 2 ለ 1 አሸንፋለች። አርበር ሆክስሃ ለአልባኒያ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በሌሎች ጨዋታዎች ኮሶቮ ስሎቫኪያን 4 ለ 3 ስትረታ ቼክ ሪፐብሊክ አየርላንድን፣ ቦሲኒያ እና ሄርዞጎቪና ዌልስን በተመሳሳይ በመለያ ምት አሸንፈዋል። ውጤቶቹን ተከትሎ ጣልያን፣ ዴንማርክ፣ ስዊድን፣ ፖላንድ ፣ ቼክ ሪፐብሊክ፣ ቦሲኒያ እና ሄርዞጎቪና እንዲሁም ኮሶቮ ለፍጻሜ ጨዋታ አልፈዋል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ ቱርኪዬ ሮማንያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ጣልያን ከቦሲኒያ እና ሄርዞጎቪና፣ ፖላንድ ከስዊድን፣ ቱርኪዬ ከኮሶቮ እና ዴንማርክ ከቼክ ሪፐብሊክ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ለዓለም ዋንጫው ለማለፍ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በጥሎ ማለፉ የሚያሸንፉ አራት ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ።
"ቪዚት ሐረር" የጎዳና ላይ የሩጫ ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ተካሄደ
Mar 27, 2026 76
ሐረር፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፡- የሹዋሊድ በዓልን ምክንያት በማድረግ "ቪዚት ሐረር" የተሰኘ የጎዳና ላይ የሩጫ ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ተካሂዷል። የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ፌስቲቫሉ፤ በርካታ የክልሉ ነዋሪዎች፣ አመራር አካላት፣ አትሌቶች፣ ታዳጊ ሕጻናት፣ ወጣቶችንና ሌሎችን አሳትፏል። የጎዳና ላይ የሩጫ ፌስቲቫሉን ያስጀመሩት የክልሉ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ተውፊቅ መሀመድ እንዳሉት፤ የሩጫ ፌስቲቫሉ አብሮነትን የሚያጠናክር ነው። የሐረሪ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙራድ አብዲ በበኩላቸው፤ የሹዋሊድ በዓልን በማስመልከት የተዘጋጀው የሩጫ ፌስቲቫል በሐረር የሚገኙ የመስኅብ ስፍራዎችን ለማስተዋወቅና እንዲጎበኙ ለማድረግ ታስቦ መዘጋጀቱን አስረድተዋል። ይህም በክልሉ የሚገኙ ጥንታዊ፣ ባህላዊና ታሪካዊ የመስኅብ ስፍራዎችን ይበልጥ ለማስተዋወቅ ይረዳል ብለዋል። በፌስቲቫሉ አሸናፊ ለሆኑ ተወዳዳሪዎች የሜዳሊያና የዋንጫ ሽልማት ተበርክቷል።
የስፖርት እንቅስቃሴ ባህልን የቀየሩት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች
Mar 27, 2026 76
በመዲናዋ የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ስራዎች የከተማውን ገጽታ በመቀየር ውብ እንድትሆን እያደረጓት ይገኛሉ። በዚህም በርካታ መዝናኛ ስፍራዎችና ስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ ነው። እነዚህ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ቀንም ሆነ ማታ አገልግሎት መስጠት የሚያስችሏቸው መሰረተ ልማቶች ተሟልተውላቸው አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ። በስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ያገኘናቸው ወጣቶች ለኢዜአ እንዳሉት፤ ማዘውተሪያዎቹ በጀመሩት የምሽት አገልግሎት ከስራ መልስ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ጤናችን እንድንጠብቅ አስችሎናል። በከተማው የምሽት አገልግሎት መስጠት ከጀመሩት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች መካከል በየካ ክፍለ ከተማ የሚገኝ 28 ሜዳ አንዱ ነው። በሜዳው ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ከሚያደርጉ ወጣቶች መካከል ያሬድ ስጦታው ከጓደኞቹ ጋር በመሆን ለበርካታ ዓመታት ስፖርታዊ እንቅስቃሴ የሚያደርጉበት ሜዳ መሆኑን ገልጿል። ሜዳው ከዚህ ቀደም ጥራቱን ያልጠበቀና ምንም ዓይነት እድሳት ያልተደረገለት እንደነበርም ያስታውሳል። አሁን ግን ሜዳው ጥራቱን የጠበቀና ምሽትን ጨምሮ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሰረተ ልማት ተሟልቶለት እስከ ምሽት እስከ 4 ሰዓት እንድንጫወት አስችሎናል ይላል። ወጣት ዳዊት ደማሙና አቤል ነጋሲ በበኩላቸው፤ የስፖርት ማዘውተሪያው የምሽት አገልግሎት መስጠት መጀመር ቀን ስራ ውለን ማታ ጊዜያችንን በስፖርት እንቅስቃሴ እንድናሳልፍ አድርጎናል ብለዋል። ይህም ከአብሮ አደግ ጓደኞቻችን ጋር ያለን ኅብረት እንድናጎለብት አስችሎናል ይላሉ። በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ ሰባት የሚገኘው የስፖርት ማዘውተሪያም በምሽት አገልግሎት እየሰጠ ነው። በዚሁ ወቅት ወጣት ተከተል ታዬ እንዳለው፤ ሜዳው ከዚህ ቀደም በአካባቢው ያልነበረና የኮሪደር ልማቱን ተከትሎ የተገነባ ነው። በተለይም በምሽት አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሰረተ ልማቶች መያዙ ማታ ከስራ መልስ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ጤናችን እንድንጠበቅ እያስቻለን ነው ብሏል። በዚህም ከእኩዮቹ ጋር ስፖርታዊ እንቅስቃሴ የሚያደርጉበት የጤና ቡድን መስርተው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጿል። የስፖርት ማዘውተሪያው አገልግሎት ከረዥም ጊዜ በኋላ ወደ ስፖርት እንድመለስ አድርጎኛል በማለት የገለጸው ደግሞ ወጣት ማይክ ብርሃኔ ነው። የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ፤ በመዲናዋ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች የስፖርት ማዘውተሪያ እጥረት ከመቅረፍ ባሻገር ለከተማዋ ተጨማሪ ድምቀት መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የከተማዋ ወጣቶችም አልባሌ ቦታ እንዳይውሉና ጤናቸውን እንዲጠብቁ በማድረግ በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ የስፖርት ማዘውተሪያዎቹ የምሽት አገልግሎት መስጠት መጀመራቸው በተለይም ነዋሪዎች ከስራ መልስ ምቹ በሆነ ሜዳ ላይ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ የሚያደርጉበት ቦታ መኖሩ በርካታ ጥቅሞችን እያስገኘ ነው ብለዋል። በቀጣይም የስፖርት ማዘውተሪያና መዝናኛዎችን የማስፋፋት እንዲሁም የወጣት ስብዕና መገንቢያ ማዕከላትን የማዘመን ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
ጃማይካ እና ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ የፍጻሜ ጨዋታ አለፉ
Mar 27, 2026 75
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም የክፍለ አህጉራት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሜክሲኮ ተካሄደዋል። ዛሬ ማለዳ በአክሮን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጃማይካ ኒው ካሌዶኒያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ባይሊ ካዳማርቴሪ በ18ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ጃማይካ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እጅሎችን በመፍጠር ከተጋጣሚዋ ኒው ካሌዶኒያ ተሽላ ተገኝታለች። ትናንት ከእኩለ ሌሊት በኋላ በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ቦሊቪያ ሱሪናምን 2 1 ረታለች። በቢቢቪኤ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሞሰስ ፓኒያጉአ በጨዋታ እና ሚጉዌል ቴርሴሮስ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሊያም ቫን ጌልደርን ለሱሪናም ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቶቹን ተከትሎ ጃማይካ እና ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ፍጻሜ አልፈዋል። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከጃማይካ እና ኢራቅ ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ መጋቢት 18 ቀን 2018 ዓ.ም በሜክሲኮ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ ያላቸው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ኢራቅ አስቀድመው ለፍጻሜው ጨዋታ ማለፋቸው ይታወቃል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ትጫወታለች
Mar 27, 2026 105
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የመጀመሪያ ጨዋታዋን ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ዛሬ ታደርጋለች። የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታ በሞሮኮ ኤል አብዲ ስታዲየም ምሽት 1 ሰዓት ላይ ይካሄዳል። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ ጁን 2027 በኬንያ ፣ ዩጋንዳና ታንዛንያ ጣምራ አዘጋጅነት ይከናወናል። በአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ 12 አገራት የደርሶ መልስ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ከጨዋታዎቹ መካከል ኢትዮጵያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር የምታደርገው ይገኝበታል። የሁለቱ ሀገራት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛሬ ይካሄዳል። ብሄራዊ ቡድኖቹ በውድድር ጨዋታዎች ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ባደረጓቸው ሁለት ጨዋታዎች በተመሳሳይ አንድ ጊዜ አሸንፈዋል። ሩሲያ እ.አ.አ በ2018 ባዘጋጀቸው 21ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የአፍሪካ ዞን ማጣሪያ ላይ ተገናኝተው ኢትዮጵያ በድምር ውጤት 3 ለ 1 በማሸነፍ ቀጣዩን ዙር መቀላቀሏ የሚታወስ ነው። በመጀመሪያው ጨዋታ ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ 1 ለ 0 ስታሸንፍ ኢትዮጵያ በመልሱ ጨዋታ 3 ለ 0 አሸንፋለች። ዮሐንስ ሳህሌ በታህሳስ ወር 2018 ዓ.ም በሁለት ዓመታት የውል ጊዜ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው በይፋ መሾማቸው ይታወቃል። አዲሱ አሰልጣኝ የመጀመሪያ ጨዋታቸውን ዛሬ ያደርጋሉ። አሰልጣኝ ዮሐንስ ለጨዋታዎቹ ጥሪ ያደረጉላቸው ተጫዋቾች ለስምንት ቀናት በአዲስ አበባ ልምምዳቸውን አድርገዋል። ብሄራዊ ቡድኑ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት ማምሻውን በኤል አብዲ ስታዲየም ማድረጉን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በ47 ዓመቱ ፓርቹጋላዊ ሪካርዶ ሞናሳንቶ የሚመራው የሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ብሄራዊ ቡድን ለጨዋታ ለአንድ ሳምንት ያህል ልምምዱን አከናውኗል። በፊፋ ወርሃዊ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ ሳኦ ቶሜ እና ፕሪንሲፔ 189ኛ ደረጃን ይዛለች። ኢትዮጵያ 147ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። ሁለቱ ብሄራዊ ቡድኖች የመልስ ጨዋታቸውን መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ያደርጋሉ። በደርሶ መልስ የሚያሸንፈው ሀገር ወደ ምድብ ድልድል ምዕራፍ ማለፉን ያረጋግጣል።
ቱርክዬ ወሳኝ ድል ተቀዳጅታለች
Mar 26, 2026 152
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የአውሮፓ የጥሎ ማለፍ የመጀመሪያ መርሐ ግብር ቱርክዬ ሮማንያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን ኢስታንቡል በሚገኘው ቱርፓስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፌርዲ ካዲኦግሉ በ53ኛው ደቂቃ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ቱርክዬ ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ውጤቱን ተከትሎ ቱርክዬ ወደ ጥሎ ማለፉ የመጨረሻ ማጣሪያ ጨዋታ አልፋለች። ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ከስሎቫኪያ እና ኮሶቮ አሸናፊ ጋር መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ትጫወታለች። የ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ጥሎ ማለፍ ቀሪ ጨዋታዎች ማምሻውን መካሄዳቸውን ይቀጥላሉ። በጥሎ ማለፉ የሚያልፉ አራት ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ።
23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ይካሄዳል
Mar 26, 2026 144
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ከመጋቢት 20 እስከ 27 ቀን 2018 ዓ.ም በሐረር ከተማ እንደሚካሄድ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ። የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ መኪዩ መሐመድ ውድድሩንና ፌስቲቫሉን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል። ሚኒስትር ዴኤታው መንግስት ለስፖርት ልማት በሰጠው ልዩ ትኩረት በአዲሱ የስፖርት ፖሊሲ አማካኝነት የባህል ስፖርቶችን ለማልማት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ሁነቱ የኢትዮጵያን ህብረ ብሄራዊ አንድነት፣ ብዝሃነት እና አብሮነት የሚተዋወቅበት መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ህይወት መሐመድ በበኩላቸው ውድድሩና ፌስቲቫሉ ህብረተሰቡን በባህል ስፖርት ተሳታፊና ተጠቃሚ ከማድረግም ባሻገር የባህል ስፖርትን ማህበረሰብ አቀፍ የማድረግ አላማ እንዳለው ገልጸዋል። በውድድርና ፌስቲቫሉ ከአፍሪካ ባህል ስፖርቶች እና ጨዋታዎች ኮንፌዴሬሽን የተጋበዙ የክብር እንግዶች እንደሚታደሙበት ጠቁመዋል። በ11 የስፖርት አይነት በሚካሄደው ውድድርና ፌስቲቫል ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ከ1500 በላይ ስፖርተኞች ይሳተፋሉ። ሁነቱ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ነው። ውድድሩና ፌስቲቫሉ "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ እንደሚካሄድ የሚኒስቴሩ መረጃ ያመለክታል።
ብሔራዊ ቡድኑ ከነገው ጨዋታ አስቀድሞ የመጨረሻ ልምምዱን አከናውኗል
Mar 26, 2026 158
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ነገ የመጀመሪያ የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታውን ታደርጋለች። ብሔራዊ ቡድኑ ጨዋታው በሚደረግበት ኤል አብዲ ስታዲየም የመጨረሻ ልምምዱን ዛሬ ማምሻውን አከናውኗል። ሁሉም ተጫዋቾች በተሟላ ጤንነት ልምምዳቸውን ሰርተው ማጠናቀቃቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የኢትዮጵያ እና ሳኦቶሜ ጨዋታ ነገ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በኤል ጀዲዳ ኤል አብዲ ስታዲየም ይከናወናል።
ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 26, 2026 68
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ድሬዳዋ ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአርባምንጭ ከተማዋ መድሃኒት ዓለሙ በ79ኛው ደቂቃ በራሷ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። የድሬዳዋ ከተማዋ መዓዛ አብደላ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጣለች። ከአምስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ድሬዳዋ ከተማ በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 10ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ ባለፉት 14 የሊጉ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ይርጋጨፌ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 4 ለ 2፣ ቦሌ ክፍለ ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 21ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከመጋቢት 28 እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም በቱርክዬ በሚከናወነው የዩኤፋ የወዳጅነት ዋንጫ ዝግጅት እና ተሳትፎ ያደርጋል። በብሔራዊ ቡድኑ ተሳትፎ ምክንያት የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ እንደሚቋረጥ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ቦሌ ክፍለ ከተማ ድል ቀንቶታል
Mar 26, 2026 82
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ቦሌ ክፍለ ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 ረቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ምህረት በቀለ ሁለቱንም ግቦች አስቆጥራለች። ምህረት አየለ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል የተመለሰው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ34 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ያሸነፋቸው ጨዋታዎች ብዛት ዘጠኝ ደርሰዋል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ባህር ዳር ከተማ በ16 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ለዩኤፋ ፍሬንድሺፕ ካፕ ውድድር ለ22 ተጫዋቾች ጥሪ ቀረበ
Mar 26, 2026 74
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በቱርክዬ ለሚከናወነው የዩኤፋ ፍሬንድሺፕ ዋንጫ ውድድር አሰልጣኝ ቻለው ለሜቻ ለ22 ተጫዋቾች ጥሪ አድርገዋል። ስመኝሽ ፍቃዱ (አዳማ ከተማ) እና ሊንጎ ኦማን (ቦሌ ክፍለ ከተማ) ጥሪ የተደረገላቸው ግብ ጠባቂዎች ናቸው። በተከላካይ መስመር አሶሬ ሃይሶ (ባህር ዳር ከተማ )፣ ፍቅርአዲስ ገዛኸኝ ( ቦሌ ክፍለ ከተማ) ፣ ለምለም አስታጥቄ (ሃዋሳ ከተማ )፣ ሳባ ኃይለሚካኤል (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ቤተልሄም መስፍን (ሃዋሳ ከተማ)፣ ከአምላክነሽ ሃንኮ (ሃዋሳ ከተማ)፣ ዝናሽ ሰለሞን (ድሬዳዋ ከተማ) እና ወርቅነሽ ዘሪሁን (ሸገር ከተማ) ጥሪ ተደርጎላቸዋል። ቱሪስት ቱንጋ (አዳማ ከተማ) ዙፋን ደፈርሻ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ሚለን ጋይም (ቦሌ ክፍለ ከተማ)፣ ሜላት ጌታቸው (ቦሌ ክፍለ ከተማ)፣ ብርሃን ኃይለስላሴ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ) እና ጋብሬላ አበበ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ) ቡድኑን እንዲቀላቀሉ ጥሪ ቀርቦላቸዋል። ታሪኳ ጴጥሮስ (ሃዋሳ ከተማ)፣ ምትኬ ብርሃኑ (ሲዳማ ቡና)፣ ቤዛዊት ንጉሴ (መቻል) ፣ ህዳት ካሱ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ሊዲያ ኢያሱ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ እና ማርያማዊት ታጠቅ (ኢትዮጵያ ስፖርት) በአጥቂ መስመር የሚገኙ ተጫዋቾች ናቸው። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ልምምዱን ከዛሬ ጀምሮ እንደሚያደርግ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር የሚያካሂደው የ’UEFA Frendship Cup’ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ውድድር በቱርክዬ አስተናጋጅነት ከመጋቢት 28 እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም ይከናወናል። በዚህ ውድድር ላይ ከተለያዩ አህጉራት የተውጣጡ ሀገራት የሚሳተፉ ሲሆን የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ጋር በፈጠረው ግንኙነት ከአፍሪካ ከሚሳተፉ ሁለት ሀገራት መካከል አንዱ መሆን ችሏል። በዚህም ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ይሳተፋል። በዚህ ውድድር ላይ አስተናጋጇ ቱርክዬን ጨምሮ ኢትዮጵያ፣ ኖርዌይ፣ ኡዝቤኪስታን፣ ኮስታሪካ፣ ፓራጓይ፣ ዩራጓይ እና ሞሮኮ ተሳታፊ እንደሚሆኑ የተረጋገጡ ቡድኖች ናቸው
ይርጋጨፌ ቡና ከ12 ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 26, 2026 61
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ይርጋጨፌ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 4 ለ 2 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ መንደሪን ክንድይሁን ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር አዳነች አስፋው እና ፍጹም ብርሃኑ ቀሪዎቹን ጎሎች ለይርጋጨፌ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አለሚ በዬቻ እና መሰረት ምክረ ለአዲስ አበባ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሁለት ግቦችን ያስቆጠረችው መንደሪን ክንድይሁን የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከ12 ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል የተመለሰው ይርጋጨፌ ቡና በ14 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 16ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዲስ አበባ ከተማ በ11 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዝግጅቱን ጀመረ
Mar 26, 2026 65
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ከደቡብ ሱዳን ጋር ለሚያደርጋቸው የመጀመርያ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች ዛሬ ልምምድ ማድረግ ጀምሯል። ማለዳ ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ልምምድ በአሰልጣኝ ራውዳ ዓሊ ጥሪ ከተደረገላቸው 23 ተጫዋቾች መካከል 16ቱ መገኘታቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ቀሪዎቹ ተጫዋቾች ከዛሬ የክለብ ጨዋታዎች በኃላ ተጠቃለው ወደ ስብስቡ እንደሚገቡም አመልክቷል። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ጨዋታዋን በሚያዚያ ወር 2018 ዓ.ም ከደቡብ ሱዳን ጋር ታደርጋለች።
ወደ ዓለም ዋንጫ የሚያልፉ ቀሪ ስድስት ሀገራት የሚለዩባቸው የማጣሪያ ጨዋታዎች
Mar 26, 2026 137
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በአሜሪካ፣ ሜክሲኮ እና ካናዳ ጣምራ አዘጋጅነት ከሰኔ 4 እስከ ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። በዓለም ዋንጫው 48 ሀገራት የሚሳተፉ ሲሆን፤ እስከ አሁን 42 ሀገራት የተሳትፎ ትኬታቸውን ቆርጠዋል። በውድድሩ ላይ የሚሳተፉ ቀሪ ስድስት ሀገራት የሚለዩባቸው የመጀመሪያ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ጥሎ ማለፍ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ይከናወናሉ። ምሽት 2 ሰዓት ላይ ቱርክዬ ከሮማንያ በቱፕራስ ስታዲየም ይጫወታሉ። የአራት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ጣልያን ከሰሜን አየርላንድ፣ ዴንማርክ ከሰሜን ሜቄዶኒያ፣ ፖላንድ ከአልባኒያ፣ ቼክ ሪፐብሊክ ከአየርላንድ፣ ዩክሬን ከስዊድን፣ ስሎቫኪያ ከኮሶቮ እና ዌልስ ከቦሲኒያ እና ሄርዞጌቪና በተመሳሳይ ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ45 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የዛሬውን ጨዋታ የሚያሸንፉ ሀገራት ለዓለም ዋንጫው ለማለፍ ወደሚደረገው የመጨረሻ ማጣሪያ ያልፋሉ። በመጨረሻው ማጣሪያ የጣልያን እና ሰሜን አየርላንድ አሸናፊ ከዌልስ እና ቦሲኒያና ሄርዜጎቪና አሸናፊ፣ የፖላንድ እና አልባኒያ አሸናፊ ከዩክሬንና ስዊድን አሸናፊ፣ የቱርክዬና ሮማኒያ አሸናፊ ከስሎቫኪያና ኮሶቮ አሸናፊ እንዲሁም የዴንማርክ እና ሰሜን ሜቄዶኒያ አሸናፊ ከቼክ ሪፐብሊክ እና አየርላንድ አሸናፊ ጋር ይጫወታሉ። የመጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጨዋታዎችን የሚያሸንፉ አራት ሀገራት ለዓለም ዋንጫ ማለፋቸውን ያረጋግጣሉ። አራቱ ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ከአውሮፓ 16 ሀገራት ይሳተፋሉ። በተያያዘም የክፍለ አህጉራት የዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ የመጀመሪያ ጨዋታዎችም ይካሄዳሉ። በማጣሪያው ላይ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ (አፍሪካ)፣ ኢራቅ (እስያ)፣ ቦሊቪያ (ደቡብ አሜሪካ)፣ ሱሪናም (ሰሜን/ማዕከላዊ አሜሪካ እና ካሪቢያን)፣ ጃማካይ (ሰሜን/ማዕከላዊ አሜሪካ እና ካሪቢያን) እና ኒው ካሌዶኒያ (ኦሽንያ) ይሳተፋሉ። በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ ያላቸው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ (48ኛ) እና ኢራቅ (55ኛ) በቀጥታ ወደ መጨረሻው የማጣሪያ ጨዋታ አልፈዋል። ቀሪዎቹ አራት ሀገራት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታቸውን በሜክሲኮ ያደርጋሉ። ቦሊቪያ ከሱሪናም ከሌሊቱ 7 ሰዓት በስታዲዩ ቢቢቪኤ፣ ኒው ካሌዶኒያ ከጃማይካ በአክሮን ስታዲየም ከጠዋቱ 12 ላይ ይጫወታሉ። የኒው ካሌዶኒያ እና ጃማይካ አሸናፊ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ የቦሊቪያ እና ሱሪናም አሸናፊ ከኢራቅ ጋር ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የመጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታቸውን ያሸነፉ ሁለት ሀገራት ለዓለም ዋንጫው ያልፋሉ።
የመውረድ ስጋት ያለባቸው ክለቦች የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Mar 26, 2026 105
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ይርጋጨፌ ቡና ከአዲስ አበባ ከተማ በአበባ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በ13ቱ ተሸንፎ በአምስቱ አቻ ወጥቷል። በ20ዎቹ ጨዋታዎች ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 31 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በ11 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ 20 ጨዋታዎች አከናውኖ ሶስት ጊዜ ድል ሲቀናው፤ በ15ቱ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 12 ግቦችን ሲያስቆጥር 41 ጎሎችን አስተናግዷል። አዲስ አበባ ከተማ በተመሳሳይ 11 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ 13ኛ ደረጃን በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ይርጋጨፌ ቡና ባለፉት 12 የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በአንጻሩ አዲስ አበባ ከተማ ካሸነፈ ከወራጅ ቀጠና ይወጣል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ድሬዳዋ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ድሬዳዋ ከተማ እስከ አሁን በሊጉ ማሸነፍ የቻለው ጨዋታ ብዛት ስድስት ነው። 11 ጊዜ ሲሸነፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 18 ግቦችን ሲያስቆጥር 31 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ21 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ 20 ጨዋታዎችን አድርጎ ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ፤ 14 ጊዜ ተሸንፏል። በአራት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 10 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 37 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት አምስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። አርባምንጭ ከተማ ባለፉት 13 ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ ላለመውረድ በሚደረገው ፉክክር ወሳኝ የሚባሉ ናቸው። ቦሌ ክፍለ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ31 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ባህር ዳር ከተማ በ16 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ቦሌ ክፍለ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ባህር ዳር ከተማ ካሸነፈ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Mar 25, 2026 87
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሲዳማ ቡናን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ህዳት ካሡ ግቦቹን አስቆጥራለች። ግቦቹን ያስቆጠረችው ህዳት ካሡ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከሁለት የአቻ ውጤቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ54 ነጥብ ከመሪው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር በነጥብ እኩል በመሆን በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በሊጉ 17ኛ ድሉንም አስመዝግቧል። የሁለቱ ቡድኖች በነጥብ እኩል መሆን የዋንጫ ፉክክሩን የበለጠ ሳቢ አድርጎታል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመቻል ጋር አንድ አቻ ተለያይቷል።
አዲስ አበባን ጽዱ፣ ውብና አረንጓዴ በማድረግ ለወጣቶች ምቹ የልማት ማዕከል የመገንባት ራዕይ በተግባር እየተረጋገጠ ነው
Mar 25, 2026 75
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ አዲስ አበባን ጽዱ፣ ውብና አረንጓዴ በማድረግ ለወጣቶች ምቹ የመዝናኛና የልማት ማዕከል የመገንባት ሥራ በተግባር እየተረጋገጠ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ በአራዳ ፓርክ የወጣቶች የኪነ-ጥበብ እና የፈጠራ ስራዎች የቀረቡበት መርሀ-ግብር አካሂዷል፡፡ የቢሮው ኃላፊ አቶ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ በዚሁ ወቅት፤ ከተማ አስተዳደሩ ወጣቶችን ታሳቢ ያደረጉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ማቀድ ብቻ ሳይሆን በተግባር በመፈጸም ውጤታማነቱን እያሳየ ይገኛል። በወንዝ ዳርቻና በኮሪደር ልማት የተገነቡ የወጣት ማዕከላት የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትልቅ ሚና በመጫወት ላይ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ በአራዳ ፓርክ የተካሄደው ወጣቶች የተሳተፉበት የባህላዊ ውዝዋዜ፣ የኪነ ጥበብ እና የፈጠራ ስራዎች መርሃ-ግብር ለዚህ ስኬት አብነት መሆኑን ጠቅሰዋል። እነዚህ ስፍራዎች ወጣቶች አብሮነታቸውንና ወንድማማችነታቸውን የሚያጠናክሩባቸው የጋራ መድረኮች ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉም ብለዋል። መሰል የማዘውተሪያ ስፍራዎች ወጣቶች በሀገራቸው ላይ ትልቅ ተስፋ እንዲሰንቁና የፈጠራ አቅማቸውን ወደ ላቀ ደረጃ እንዲያሸጋግሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱ አስረድተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች ማህበር ፕሬዝዳንት ምንያህል ጌታቸው እንዳለውም፣ አዲስ አበባ እንደ ስሟ እያበበች መሆኗን ገልጿል። የተገነቡት ማራኪ የመዝናኛ ስፍራዎች መንግስት ለወጣቱ ትውልድ የሚሰጠውን ልዩ ትኩረት የሚያሳዩና ተጠቃሚነትን በተጨባጭ ያረጋገጡ ስኬቶች መሆናቸውን ተናግሯል። ወጣት አርሴማ ሽመልስ በበኩሏ ቀደም ባሉት ጊዜያት በከተማዋ በቂ የወጣቶች መዝናኛ ስፍራዎች እንዳልነበሩ አስታውሳ አሁን የተገነቡት ስፍራዎች ለዓይን ማራኪ ከመሆናቸው ባለፈ፣ ወጣቶች ተሰጧቸውን የሚያሳዩበት ሰፊ ዕድል ፈጥሯል ብላለች፡፡
የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነጥብ ጣለ
Mar 25, 2026 84
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና መቻል አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ንግሥት በቀለ በ66ኛው ደቂቃ ባስቆጠረችው ጎል ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሪ ሆኗል። ጨዋታው በንግድ ባንክ አሸናፊነት ተጠናቀቀ ሲባል ቱሪስት ለማ በ91ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፈችው ግብ መቻል ወሳኝ አንድ ነጥብ አግኝቷል። ለመቻል ግቡን ያስቆጠረችው ቱሪስት ለማ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነጥቡን ወደ 54 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማስፋት እድል አልተጠቀመበትም። መቻል በ45 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ በሊጉ አምስተኛ ተከታታይ ድሉን የማስመዝገብ ሙከራው አልተሳካም።
የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታዎች
Mar 25, 2026 95
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሠዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመቻል በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በ17ቱ ድል ሲቀናው አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 58 ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ንግድ ባንክ በ53 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በሊጉ እስከ አሁን 20 ጨዋታዎች አከናውኖ 13 ጊዜ ሲያሸንፍ፤ በሁለቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 37 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያገናኝ 11 ግቦች ተቆጥረውበታል። መቻል በ44 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ መሪነቱን ያጠናክራል። መቻል ካሸነፈ በሊጉ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። በ20ኛ ሳምንት ከቦሌ ክፍለ ከተማ በተደረገው ጨዋታ በቀይ ካርድ የወጣችው የመቻል አጥቂ ሴናፍ ዋቁማ በዛሬው ጨዋታ አትሰለፍም። ሁለቱ ቡድኖች በጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። ቡድኖቹ በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት የሊጉ ጨዋታ ያለ ግብ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ20 የሊጉ ጨዋታዎች በ16ቱ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ20ዎቹ ጨዋታዎች ላይ 44 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 11 ግቦች ተቆጥረውበታል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ51 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በውድድር ዓመቱ 20 ጨዋታዎች አድርጎ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ፤ በተመሳሳይ በስምንት ጨዋታዎች ሽንፈት አጋጥሞታል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 20 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 25 ጎሎችን አስተናግዷል። ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ ማግኘት ለቡድኑ የዋንጫ ፉክክር ወሳኝ ነው። በ20ኛ ሳምንት ከድሬዳዋ ከተማ ጋር አንድ አቻ የተለያየው ሲዳማ ቡና ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። የዛሬ ጨዋታዎች በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ የሚባሉ ናቸው።