ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሃዋሳ ከተማ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል
Nov 14, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሁለት ጨዋታዎች በአበባ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ሃዋሳ ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ይጫወታሉ። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አራት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በጨዋታዎቹ ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ በሊጉ ያከናወናቸውን አምስት ጨዋታዎች አሸንፏል። 13 ግቦችን ሲያስቆጥር የተቆጠረበት አንድ ግብ ብቻ ነው። ቡድኑ በ15 ነጥብ ሊጉን እየመራ ይገኛል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት ጥሩ ጅማሮ ያሳዩት ሁለቱ ክለቦች በጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና ከአዲስ አበባ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሲዳማ ቡና በሊጉ ካደረጋቸው አራት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ሲዳማ ቡና አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በስድስት ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል አንዱን ሲያሸንፍ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በጨዋታዎቹ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር 11 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በሶስት ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ቀሪ ስምንት ክለቦች ቀጣዩን ዙር ተቀላቅለዋል
Nov 13, 2025 82
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና አዳማ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። አቡበከር አዳሙ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። አህመድ ሁሴን ለአዳማ ከተማ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ባህር ዳር ከተማ ሸገር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አማኑኤል ገብረሚካኤል እና ግርማ ዲሳሳ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ በሬድዋን ሸረፋ ግብ ሃዋሳ ከተማን 1 ለ 0 ረቷል። በተመሳሳይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን በመለያ ምት 4 ለ 2 አሸንፏል። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል። በሌሎች ጨዋታዎች አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ 2 ለ 1 እና ቢሾፍቱ ከተማ ደሴ ከተማን 1 ለ 0 ሲያሸንፉ ንብ እግር ኳስ ክለብ የካ ክፍለ ከተማን ደብረብርሃን ከተማ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማን በመለያ ምት ማሸነፍ ችለዋል። ዛሬ እና ትናንት የተደረጉ ጨዋታዎችን ተከትሎ 16 ክለቦች ለሶስተኛው ዙር አልፈዋል። ኢትዮጵያ መድን፣ ቤንች ማጂ ቡና፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ፣ አርባምንጭ ከተማ፣ ቦዲቲ ከተማ፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ መቻል፣ ነጌሌ አርሲ፣ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ፣ ድሬዳዋ ከተማ፣ ባህር ዳር ከተማ፣ ደብረብርሃን ከተማ፣ ንብ እግር ኳስ ክለብ፣ ቢሾፍቱ ከተማ፣ ኢትዮጵያ ቡና እና ሲዳማ ቡና 16ቱን የተቀላቀሉ ክለቦች ናቸው። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ ከውድድሩ ተሰናብቷል። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር በቀጣይ በሚገለጽ ቀን እና ቦታ ይካሄዳል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አዳማ ከተማ ድል ቀንቶታል
Nov 13, 2025 69
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር አዳማ ከተማ ቦሌ ክፍለ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቱሪስት ቱንጋ እና ነጻነት መና የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ምህረት አየለ ለቦሌ ክፍለ ከተማ ብቸኛውን ጎል አስቆጥራለች። ውጤቱን ተከትሎ አዳማ ከተማ በሊጉ ሁለተኛ ድሉን ሲያስመዘግብ ቦሌ ክፍለ ከተማ አራተኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል። ቀን ላይ በተደረገ ጨዋታ መቻል ይርጋጨፌ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ መቻል ይርጋጨፌ ቡናን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል
Nov 13, 2025 65
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቻል ይርጋጨፌ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ በቂላ ስታዲየም በተካሄደ ጨዋታ የይርጋጨፌ ቡናዋ ሰላም ፀጋዬ በ91ኛው ደቂቃ በራሷ ግብ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። የመቻሏ ሰናይት ሸጎ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ አራተኛ ድሉን ያሳካው መቻል በ13 ነጥብ ደረጃውን ከአራተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ይርጋጨፌ ቡና በአራት ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በአሁኑ ሰዓት አዳማ ከተማ ከቦሌ ክፍለ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን እያደረጉ ነው።
መቻል፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ ነጌሌ አርሲ እና ቦዲቲ ከተማ በኢትዮጵያ ዋንጫ ወደ ሶስተኛ ዙር አለፉ
Nov 13, 2025 73
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ጨዋታዎች ዛሬም እየተካሄዱ ነው። በሃዋሳ አርቴፊሻል ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ መቻል ምድረገነት ሽሬን 3 ለ 0 አሸንፏል። አብዱልከሪም ወርቁ በጨዋታ፣ ዮሴፍ ታረቀኝ በፍጹም ቅጣት እና የምድረገነት ሽሬው ክብሮም ብርሃነ በራሱ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሌላኛው መርሃ ገብር ነጌሌ አርሲ ሀዲያ ሆሳዕናን በመለያት ምት 8 ለ 7 አሸንፏል። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሀቢብ ከማል ለነጌሌ አርሲ፣ ብሩክ በየነ ለሀዲያ ሆሳዕና ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ ፋሲል ከነማን በአሸናፊ ሀፍቱ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል። ቦዲቲ ከተማ ሃላባ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በጅማ ስታዲየም በተደደረገው ጨዋታ አጥናፉ ቡሸና የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። መቻል፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ ነጌሌ አርሲ እና ቦዲቲ ከተማ 16ቱን ተቀላቅለዋል። ቀሪ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች ዛሬ ከሰዓት በኋላ ይካሄዳሉ። ትናንት በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን፣ አርባምንጭ ከተማ፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ቤንጅ ማጂ ቡና ወደ ሶስተኛ ዙር ማለፋቸው ይታወቃል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ ሁለተኛ ዙር ቀሪ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ
Nov 13, 2025 83
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ዛሬ 12 ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየም ሀዲያ ሆሳዕና ከነጌሌ አርሲ ከረፋዱ 4 ሰዓት፣ ባህር ዳር ከተማ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ። ምድረገነት ሽሬ ከመቻል ከረፋዱ 4 ሰዓት፣ ሐረር ከተማ ከአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ንብ እግር ኳስ ክለብ ከየካ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት በሃዋሳ አርቴፊሻል ስታዲየም የሚካሄዱ ጨዋታዎች ናቸው። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም መቀሌ 70 እንደርታ ከፋሲል ከነማ ከረፋዱ 4 ሰዓት፣ ድሬዳዋ ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። ሃላባ ከተማ ከቦዲቲ ከተማ ከቀኑ 4 ሰዓት፣ ደብረብርሃን ከተማ ከአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ቢሾፍቱ ከተማ ከደሴ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት በጅማ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ትናንት በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን፣ አርባምንጭ ከተማ፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ቤንጅ ማጂ ቡና ወደ ሶስተኛ ዙር ማለፋቸው ይታወቃል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ በወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የ2 ለ 0 አስተናግዶ ከኢትዮጵያ ዋንጫ ተሰናብቷል። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሚያሸንፍ ቡድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ
Nov 13, 2025 66
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት መቻል ከይርጋጨፌ ቡና ይጫወታሉ። መቻል በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። አንድ ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በ10 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በውድድር ዓመቱ ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አንድ ጨዋታ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ ነጥብ ተጋርቷል። ይርጋጨፌ በአራት ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። መቻል በአምስተኛ ሳምንት አርባምንጭ ከተማን 2 ለ 0 ሲያሸንፍ ይርጋጨፌ ቡና ከአዳማ ከተማ አንድ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር አዳማ ከተማ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዳማ ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው አምስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ አሸንፎ ሶስት ጊዜ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በአራት ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል በሁለቱ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። ቡድኑ በስድስት ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። በአምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር አዳማ ከተማ ከይርጋጨፌ ቡና አንድ አቻ ሲለያይ ቦሌ ክፍለ ከተማ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የ3 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
የኢትዮጵያ ዋንጫ የወቅቱ አሸናፊ ወላይታ ድቻ ከውድድሩ ተሰናበተ
Nov 12, 2025 113
አዲስ አበባ፤ ህዳር 2/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ወላይታ ድቻን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፍሬው ሰለሞን እና ጋናዊው ኮንኮኒ ሃፊዝ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ወደ ሶስተኛ ዙር አልፏል። በአንጻሩ የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ ከኢትዮጵያ ዋንጫ ተሰናብቷል። በሌላኛው መርሃ ግብር አርባምንጭ ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን በመለያ ምት 5 ለ 4 በማሸነፍ ቀጣዩን ዙር ተቀላቅሏል። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ግብ አቻ በመለያየታቸው ነው ወደ መለያ ምት ያመሩት። ቀን ላይ በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን ኢትዮ ኤሌክትሪክን፣ ቤንች ማጂ ቡና ጋሞ ጨንቻን በተመሳሳይ 1 ለ 0 በማሸነፍ 16ቱን ተቀላቅለዋል። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ነገም ሲቀጥል 12 ጨዋታዎች ይደረጋሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሸገር ከተማ ድሬዳዋ ከተማን አሸነፈ
Nov 12, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ህዳር 2/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ሸገር ከተማ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሰርካለም ባሳ እና የድሬዳዋ ከተማዋ ብዙነሽ እሸቱ በራስዋ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። መዓዛ አብደላ ለድሬዳዋ ከተማ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ድሉን ተከትሎ አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በ12 ነጥብ ደረጃውን ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በሶስት ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። የስድስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ህዳር 7 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በተያያዘም ዛሬ በተደረገ የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አርባምንጭ ከተማን 5 ለ 1 አሸንፏል።
ኢትዮጵያ መድን እና ቤንች ማጂ ቡና በኢትዮጵያ ዋንጫ ወደ ቀጣዩ ዙር አለፉ
Nov 12, 2025 93
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦ የ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር የመጀመሪያ ጨዋታዎች ዛሬ መካሄድ ጀምረዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን በአማኑኤል ኤርቦ ግብ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 1 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ አርቴፊሻል ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሃ ግብር ቤንች ማጂ ቡና ጋሞ ጨንቻን 1 ለ 0 ረቷል። ፅዮን ተስፋዬ ለቤንች ማጂ ቡና ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቶቹን ተከትሎ ኢትዮጵያ መድን እና ቤንች ማጂ ቡና በኢትዮጵያ ዋንጫ የመጨረሻውን 16 የተቀላቀሉ የመጀመሪያ ቡድኖች ሆነዋል። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ከሰዓትም ሲቀጥል የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም፣ አርባምንጭ ከተማ ከቅዱስ ጊዮርጊስ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተመሳሳይ ከቀኑ 9 ሰዓት ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድል ቀንቶታል
Nov 12, 2025 92
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሶስተኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አርባምንጭ ከተማን 5 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ምርቃት ፈለቀ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ እፀገነት ግርማ፣ ንግስት በቀለ እና መሳይ ተመስገን ቀሪዎቹን ግቦች አስቆጥረዋል። ድንቅነሽ በቀለ ለአርባምንጭ ከተማ ብቸኛውን ጎል አስቆጥራለች። የንግድ ባንኳ እፀገነት ግርማ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በዘጠኝ ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ምክንያት ከሲዳማ ቡና እና ሸገር ከተማ ያላደረጋቸውን ተስተካካይ ጨዋታዎች በቀጣይ በሚገለጹ ቀናት የሚያደርግ ይሆናል። በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በአንድ ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። በተያያዘም የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት ዛሬ ከቀኑ 7 ሰዓት ሸገር ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በሚያደርጉት ጨዋታ ይጀመራል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ ሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ዛሬ እና ነገ ይካሄዳል
Nov 12, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ ሁለተኛ ዙር የመጀመሪያ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከቀኑ 9 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየም ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከኢትዮጵያ ከረፋዱ 4 ሰዓት፣ አርባምንጭ ከተማ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። ቤንች ማጂ ቡና ከጋሞ ጨንቻ በሃዋሳ አርቴፊሻል ስታዲየም ከረፋዱ 4 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ነገ በኢትዮጵያ ዋንጫ 12 ጨዋታዎች ይከናወናሉ። በመጀመሪያው ዙር ውድድር የከፍተኛ ሊግ ክለቦች ብቻ የተሳተፉ ሲሆን አሸናፊ ቡድኖች በሁለተኛው ዙር ከኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ቡድኖች ጋር በመቀላቀል ይጫወታሉ። ወላይታ ድቻ የወቅቱ የኢትዮጵያ ዋንጫ አሸናፊ ነው። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሚያሸንፍ ቡድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል
Nov 12, 2025 74
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የአምስተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሸገር ከተማ እና ድሬዳዋ ከተማ ይጫወታሉ። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 7 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳል። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። ቡድኑ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በዘጠኝ ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንዱን ብቻ ነው። በቀሪ አራት ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ድሬዳዋ ከተማ በሶስት ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው ሸገር ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ፣ ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። በአራተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሸገር ከተማ አዲስ አበባ ከተማን 3 ለ 0 ሲያሸንፍ ድሬዳዋ ከተማ በሃዋሳ ከተማ የ2 ለ 0 አስተናግዷል። የስድስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ህዳር 7 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በተያያዘም የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሶስተኛ ሳምንት ተስተካካይ ጨዋታውን ዛሬ ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ከአርባምንጭ ከተማ ያደርጋል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ምክንያት በሊጉ የመጀመሪያ ሶስት ጨዋታዎቹን አላደረገም። ጨዋታዎቹም በተስተካካይ መርሃ ግብርነት ተይዘዋል። ከተስተካካይ ጨዋታዎቹ የመጀመሪያውን ከአርባ ምንጭ ከተማ ጋር ያደርጋል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በስድስት ነጥብ አምስተኛ፣ አርባምንጭ ከተማ በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። ንገድ ባንክ ቀሪ ተስተካካይ ጨዋታዎቹን ከሲዳማ ቡና እና ሸገር ከተማ ጋር በቀጣይ በሚገለጹ ቀናት የሚያደርግ ይሆናል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ15 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን ዳግማዊ ሰለሞን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በዘጠኝ ጎሎች ትመራለች። ብርቄ አማረ ከመቻል እና መሳይ ተመስገን ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተመሳሳይ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ይከተላሉ።
በተጠባቂው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ሊቨርፑልን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Nov 10, 2025 201
አዲስ አበባ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ሊቨርፑልን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሊንግ ሃላንድ፣ ዠርሚ ዶኩ እና ኒኮ ጎንዛሌዝ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አርሊግ ሃላንድ በጨዋታው ያገኘውን የፍጹም ቅጣት ምት አምክኗል። ሲቲ በጨዋታው ከተጋጣሚው በተሻለ ለግብ የቀረቡ እድሎችን ፈጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ በሊጉ ሰባተኛ ድሉን በማስመዝገብ በ22 ነጥብ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ዝቅ ብሏል። በአንጻሩ በሊጉ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሊቨርፑል በ18 ነጥብ ወደ ስምንተኛ ደረጃ ወርዷል። አርሊንግ ሃላንድ በሊጉ ያስቆጠረችውን ጎሎች ብዛት ወደ 12 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን አጠናክሯል። በተያያዘም ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች አስቶንቪላ ቦርንማውዝን 4 ለ 0 ሲረታ ብሬንትፎርድ ኒውካስትል ዩናይትድን ኖቲንግሃም ፎረስት ሊድስ ዩናይትድን በተመሳሳይ 3 ለ 1 አሸንፈዋል። ክሪስታል ፓላስ ከብራይተን ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ከዓለም አቀፍ የብሄራዊ ቡድኖች ጨዋታ መልስ ከሁለት ሳምንት በኋላ በ12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ይመለሳል።
መቻል እና ፋሲል ከነማ ነጥብ ተጋርተዋል
Nov 9, 2025 182
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 30/2018(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቻል እና ፋሲል ከነማ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተደርጓል። ሁለቱ ቡድኖች በማሸነፍ የሊጉን መሪነት ከሲዳማ ቡና የመረከብ እድላቸውን ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል። በሌላ ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ያሬድ ብሩክ ለሃዋሳ ከተማ፣ አዲስ ግደይ ለንግድ ባንክ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሀዲያ ሆሳዕና እና ሸገር ከተማ በተመሳሳይ አንድ አቻ ወጥተዋል። ብሩክ በየነ ለሀዲያ ሆሳዕና፣ ሄኖክ አዱኛ በፍጹም ቅጣት ምት ለሸገር ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ቀን ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ አዳማ ከተማ በነቢል ኑሪ ጎል ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የአምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የስድስተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር በኋላ ከህዳር 12 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እንደሚካሄድ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል። በሌላ በኩል የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተደርገዋል። ይርጋጨፌ ቡና እና አዳማ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። መንደሪን ክንድሁን ለይርጋጨፌ፣ አህላም ሲራጅ ለአዳማ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ባህር ዳር ከተማ ከሲዳማ ቡና ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተለያይተዋል።
የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ተሳታፊዎች ቁጥር እንዲጨምር አግዟል
Nov 9, 2025 254
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 30/2018(ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ተሳታፊዎችን ቁጥር በመጨመር በደመቀና በምቹ ሁኔታ እንዲካሄድ ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መስራች አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረሥላሴ ገለጸ። በዓለም የአትሌቲክስ ውድድር የገዘፈ ስም ባለው አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ በ1994 ዓ.ም የተመሰረተው ታላቁ ሩጫ፤ እስከ 2017 ዓ.ም ድረስ በድምሩ ወደ 700 ሺህ የሚጠጉ ተሳታፊዎችን ማስተናገዱን መረጃዎች ያሳያሉ። የመጀመሪያው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከ10 ሺህ ያነሱ ተሳታፊዎች የነበሩት ሲሆን፤ ባለፉት ዓመታት ውድድሩ 50 ሺህ የሚጠጉ ተሳታፊዎችን አስተናግዷል። በአፍሪካ ትልቁ የጎዳና ላይ ሩጫ እንደሆነ የሚነገርለት ውድድር፤ ከኢትዮጵያውን ባሻገር ከተለያዩ ዓለም ክፍሎች የሚመጡ የውጪ አገራት ዜጎችም የሚሳተፉበት ሆኗል። በተለያያ ወቅት የዓለም ታላላቅ አትሌቶች ውድድሩን በክብር እንግድነት በማስጀመር የተሳተፉ ሲሆን፤ ለአብነትም ፖል ቴርጋት፣ ገብርኤል ዛቦ፣ ካሮሊና ክሉፍት ፣ ዴቭ ሞርክሩፍት እና ፓውላ ራድክሊፍ ይጠቀሳሉ፡፡ በውድድሩ ሃይሌ ገብረስላሴ፣ ስለሺ ስህን፣ ጸጋዬ ከበደ፣ ብርሃኔ አደሬ፣ ወርቅነሽ ኪዳኔና ጥሩነሽ ዲባባ ማሸናፋቸው ይታወሳል፡፡ አትሌት ሻለቃ ኃይሌ ገብረሥላሴ ከኢዜአ ጋር ባደረገው ቆይታ እንደገለጸው፤ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ተተኪ አትሌቶችን ከማፍራት ባለፈ ኢትዮጵያ ትላልቅ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን ማስተናገድ እንደምትችል እያሳየ ይገኛል። በየዓመቱ በአዲስ አበባ የሚካሄደው ውድድር የኢትዮጵያን ገጽታ በማስተዋወቅ የቱሪዝም ፍሰት እንዲጨምር የበኩሉን አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ገልጿል። የውድድሩ ተሳታፊዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን ያነሳው አትሌት ሻለቃ ኃይሌ፤ በተለይ የኮሪደር ልማቱ ውድድሩ ያማረና የደመቀ እንዲሆን ማድረጉን ተናግሯል። የታላቁ ሩጫ ኦፕሬሽን ዳይሬክተር ዳግም ተሾመ በበኩሉ፤ የኮሪደር ልማቱ የውድድሩ ተሳታፊዎች ቁጥር እንዲጨምር ማድረጉን ተናግሯል። አብዛኛዎቹ የከተማዋ መንገዶች ከኮሪደር ልማቱ በፊት ለእግረኞች የተለየ መሄጃ የሌላቸውና ለስፖርታዊ እንቅስቃሴ ምቹ እንዳልነበሩ አስታውሷል፤ በዚህም ለተወዳዳሪዎች ደህንነት ሲባል በየዓመቱ የተሳታፊዎችን ቁጥር በአንድ ሺህ ወይም በሁለት ሺህ ብቻ ለመጨመር ተገደው መቆየታቸውን አስታውቋል። የኮሪደር ልማቱ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን በተለይም የመሮጥ ባህልን ለማስፋፋት እና ሰፊ ህዝብ የሚሳተፍባቸውን ውድድሮች ለማዘጋጀት ከፍተኛ አቅም እየፈጠረ መሆኑን ገልጿል። የኮሪደር ልማቱ ለስፖርቱ የሚያገለግሉ መንገዶችን በመያዙ የታላቁ ሩጫ ውድድር ተሳታፊዎችን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ እንዳስቻለ ተናግሯል። ይህን ተከትሎ በዘንድሮው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ መርኃ ግብር 55 ሺህ ተሳታፊዎች እንደሚወዳደሩ አዘጋጆቹ አስታውቀዋል።
አዳማ ከተማ በሊጉ ተከታታይ ድሉን አስመዘገበ
Nov 9, 2025 158
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 30/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር አዳማ ከተማ ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ነቢል ኑሪ በ58ኛው ደቂቃ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። የኢትዮጵያ ቡናው በፍቃዱ አለማየሁ በ73ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። አዳማ ከተማ በሊጉ ተከታታይ ድሉን በማስመዝገብ በዘጠኝ ነጥብ ደረጃውን ከስምንተኛ ወደ ሰባተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ቡና በአራት ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ይርጋጨፌ ቡና ከአዳማ ከተማ ባህር ዳር ከተማ ከሲዳማ ቡና ይጫወታሉ
Nov 9, 2025 140
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት ዛሬ በሚደረጉ ጨዋታዎች ይጠናቀቃል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ይርጋጨፌ ቡና ከአዳማ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። አንድ ጊዜ ሲሸንፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በጨዋታዎቹ ምንም ግብ አላስቆጠረም። በአንጻሩ አራት ግቦችን አስተናግዷል። ይርጋጨፌ ቡና በሶስት በነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ በበኩሉ እስከ አሁን በውድድር ዓመቱ ካካሄዳቸው አራት ጨዋታዎች መካከል አንዱን ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። ቡድኑ አንድ ግብ ሲያስቆጥር ስምንት ግቦች ተቆጥሮበታል። አዳማ ከተማ በተመሳሳይ ሶስት ነጥብ ባለበት የግብ እዳ ምክንያት 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በሌላኛው መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባህር ዳር በሊጉ ካደረጋቸው አራት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለ አንድ ጊዜ ብቻ በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ሽንፈትን አስተናግዷል። ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አምስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በሶስት ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ሲዳማ ቡና በሊጉ ካደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። አምስት ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ ሁለት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት ዛሬ በሚካሄዱ ጨዋታዎች ይጠናቀቃል
Nov 9, 2025 104
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 30/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዳማ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። አንድ ግብ ሲያስቆጥር ምንም ጎል አላስተናገደም። አቻ የወጣባቸው ጨዋታዎች ያለ ምንም ግብ የተጠናቀቁ ናቸው። ቡድኑ በስድስት ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና እስከ አሁን ባካሄዳቸው አራት ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው እንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦች ተቆጥሮበታል። ቡናማዎቹ በአራት ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። ጨዋታው አዳማ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ፣ ኢትዮጵያ ቡና ከአራተኛ ሳምንት ሽንፈቱ በኋላ ወደ ድል ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። ሸገር ከተማ ከሀዲያ ሆሳዕና ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ያደርጋሉ። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በአራት ነጥብ 13ኛ፣ ሀዲያ ሆሳዕና በሁለት ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዘዋል። ሸገር ከተማ በአራተኛ ሳምንት ቅዱስ ጊዮርጊስን በማሸነፍ የመጀመሪያ ድሉን ማስመዝገቡ የሚታወስ ነው። ሀዲያ ሆሳዕና በሊጉ እስከ አሁንም ምንጭ ጨዋታ አላሸነፈም። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ሃዋሳ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። በሊጉ ሃዋሳ ከተማ በዘጠኝ ነጥብ አምስተኛ፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአምስት ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዘዋል። ሃዋሳ ከተማ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ድል ቀንቶታል። የ2016 ዓ.ም የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ድሉን ድሬዳዋ ከተማን በአራተኛ ሳምንት 2 ለ 0 በማሸነፍ ማስመዝገቡ ይታወቃል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ መቻል ከፋሲል ከነማ ምሽት 12 ሰዓት ላይ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። መቻል እና ፋሲል ከነማ በተመሳሳይ 10 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ሶስተኛና አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። የሚያሸንፈው ቡድን የሊጉ መሪ ይሆናል።
ማንቺስተር ሲቲን ከሊቨርፑል የሚያገናኘው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የዛሬ መርሃግብር
Nov 9, 2025 123
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 30/2018(ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ሲቲ እና ሊቨርፑል የሚያደርጉት ጨዋታ የተመልካችን ቀልብ ስቧል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 1 ሰዓት ከ30 ላይ በኢትሃድ ስታዲየም ይደረጋል። ማንችስተር ሲቲ በሊጉ እስከ አሁን ባካሄዳቸው 10 ጨዋታዎች 6 ጊዜ ሲያሸንፍ 3 ጊዜ ተሸንፎ በአንዱ ደግሞ አቻ በመውጣት 20 ግቦችን ሲያስቆጥር 8 ጎሎችን አስተናግዷል። በ54 ዓመቱ ስፔናዊ ፔፕ ጋርዲዮላ የሚመራው ማንችስተር ሲቲ በ19 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሊቨርፑል በውድድር ዓመቱ ባደረጋቸው 10 ጨዋታዎች 6 ጊዜ ድል ሲቀናው 4 ጊዜ ሽንፈት አስተናግዶ 18 ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎችን አስተናግዷል። በ47 ዓመቱ ኔዘርላንዳዊ አርን ስሎት የሚሰለጥነው ሊቨርፑል በ18 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በሁሉም ውድድሮች እስከ አሁን 198 ጊዜ የተገናኙ ሲሆን ሊቨርፑል 95 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ሲይዝ ማንችስተር ሲቲ 50 ጊዜ ሲያሸንፍ 53 ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። በፕሪሚየር ሊጉ 56 ጊዜ ተገናኝተው ሊቨርፑል 23 ጊዜ ሲያሸንፍ ማንችስተር ሲቲ 12 ጊዜ ድል ቀንቶታል። 21 ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥተዋል። ሊቨርፑል እና ማንችስተር ሲቲ በሊጉ የሚያደርጉት ፉክክር ከእ.አ.አ 2010 አጋማሽ አንስቶ በየጊዜው እያደገና እየጋለ መጥቷል። ማንችስተር ሲቲ ከባለፈው ዓመት ደካማ ብቃት በኋላ በዘንድሮው የውድድር ዓመት አጀማመሩን በማሳመር ጥሩ ግስጋሴ እያደረገ ይገኛል። ተጋጣሚው ሊቨርፑል ጅማሮው ጥሩ ቢሆንም አራት ተከታታይ ሽንፈቶችን ማስተናገዱ ያልተጠበቀ ነበር። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ በዘጠነኛ ሳምንት መርሃ ግብር አስቶንቪላን በመርታት ወደ አሸናፊነት ተመልሷል። የዛሬው ጨዋታ ለሁለቱም ቡድኖች በዋንጫው ፉክክር ውስጥ ለመቆየት ወሳኝ የሚባል ነው። የ40 ዓመቱ ክሪስ ካቫናግ የሁለቱን ቡድኖች ወሳኝ ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ክሪስታል ፓላስ ከብራይተን፣ አስቶንቪላ ኮቦርንማውዝ፣ ብሬንትፎርድ ከኒውካስትል ዩናይትድ እና ኖቲንግሃም ፎረስት ከሊድስ ዩናይትድ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።