ቀጥታ፡
ስፖርት
ግብጽ የወቅቱን የአፍሪካ ዋንጫ ባለቤት ኮትዲቯር በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቀለች
Jan 11, 2026 65
አዲስ አበባ፤ ጥር 2 /2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ግብጽ ኮትዲቯርን 3 ለ 2 አሸንፋለች። ማምሻውን በአጋዲር ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኦማር ማርሙሽ፣ ራሚ ራቢያ እና መሐመድ ሳላህ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጉዌላ ዱዌ እና የግብጹ አህመድ አቡ ኤል ፎቱህ በራሱ ላይ ለኮትዲቯር ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ግብጽ ግልጽ የግብ እድሎችን በመፍጠር፣ ኮትዲቯር በኳስ ቁጥጥር የተሻሉ ነበሩ። ኮትዲቯር በጨዋታው ማብቂያ ላይ ተጭና ብትጫወትም ግብ ማስቆጠር አልቻለችም። የግብጹ መሐመድ ሳላህ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ አራት ከፍ አድርጓል። ድሉን ተከትሎ ግብጽ ግማሽ ፍጻሜ የገባች የመጨረሻዋ ሀገር ሆናለች። በግማሽ ፍጻሜው ከሴኔጋል ጋር የምታደርገው ጨዋታ ከወዲሁ ትኩረትን ስቧል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ኮትዲቯር የአፍሪካ ዋንጫ ክብሯን የመጠበቅ ጉዞዋ ሩብ ፍጻሜው ላይ ተገቷል። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ናይጄሪያ ከአዘጋጇ ሞሮኮ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ረቡዕ ጥር 6 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳሉ።
ኢትዮጵያ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቀቀች
Jan 10, 2026 99
አዲስ አበባ፤ ጥር 2 /2018 (ኢዜአ)፦ 46ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ማምሻውን በአሜሪካ ፍሎሪዳ ተካሄዷል። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በአምስት ርቀቶች በሁለቱም ጾታዎች በአጠቃላይ 20 አትሌቶችን አሳትፋለች። 10 ኪሎ ሜትር አዋቂ ወንዶች፣ 10 ኪሎ ሜትር አዋቂ ሴቶች፣ ከ20 ዓመት በታች ወንዶች 8 ኪሎ ሜትር፣ ከ20 ዓመት በታች ሴቶች 6 ኪሎ ሜትር እና ድብልቅ ሪሌይ (4 በ 2 ኪሎ ሜትር) ኢትዮጵያ የተሳተፈችባቸው ርቀቶች ናቸው። የዛሬ ውድድሮችን ተከትሎ ኢትዮጵያ በሶስት የወርቅ፣ ሁለት የብር እና ሁለት የነሐስ በድምሩ ሰባት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ኬንያን ተከትላ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ከ20 ዓመት በታች ሴቶች የስድስት ኪሎ ሜትር ውድድር አትሌት ማርታ ዓለማየሁ በ18 ደቂቃ 52 ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት ለኢትዮጵያ በሻምፒዮናው የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። ኢትዮጵያ በአዋቂ የ10 ኪሎ ሜትር ወንዶች እና ሶሴቶች በቡድን ሁለት የወርቅ ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በአዋቂ 10 ኪሎ ሜትር ወንድ ፍጻሜ አትሌት በሪሁ አረጋዊ ሁለተኛ በመውጣት የብር ሜዳሊያ አግኝቷል። አትሌት ወሰኔ አሰፋ ከ20 በታች ሴቶች የስድስት ኪሎ ሜትር ውድድር ሁለተኛ በመውጣት የብር ሜዳሊያ ባለቤት ሆናለች። በ10 ኪሎ ሜትር ሴቶች አትሌት ሰናይት ጌታቸው እና በድብልቅ ሪሌይ (ዱላ ቅብብል) የነሐስ ሜዳሊያዎች ተገኝተዋል። ኬንያ ሶስት የወርቅ፣ አራት የብር እና ሁለት የነሐስ በድምሩ ዘጠኝ ሜዳሊያዎችን በማግኘት አንደኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ዩጋንዳ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። አውስትራሊያ፣ ፈረንሳይ፣ ጃፓን እና አሜሪካ ሌሎች ሜዳሊያ ሰንጠረዥ ውስጥ የገቡ ሀገራት ናቸው። ኢትዮጵያ በሻምፒዮና ተሳትፎ ታሪኳ የዘንድሮውን ጨምሮ 112 የወርቅ፣ 123 ብር እና 67 የነሐስ በድምሩ 302 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ከኬንያ በመቀጠል ስኬታማዋ ሀገር ናት። ኬንያ የዘንድሮውን ጨምሮ ኬንያ 160 ወርቅ፣ 114 የብር እና 80 የነሐስ በድምሩ 354 ሜዳሊያዎችን በማግኘት የበላይነቱን ይዛለች።
የስፖርት ቱሪዝምን በማጠናከር የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎችን ማስተዋወቅ ይገባል
Jan 10, 2026 64
ደብረ ብርሃን ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ የስፖርት ቱሪዝምን በመጠቀም በየአካባቢው ያሉ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎችን የማስተዋወቅ ስራ ሊጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ። በአማራ ክልል በደብረ ብርሃን ከተማ በነገው ዕለት በሚካሄደው የታላቁ ሩጫ ላይ የሚሳተፉ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት የአንኮበር ቤተ መንግስትን ጎብኝተዋል።   በጉብኝቱ ላይ የተሳተፉት በቱሪዝም ሚኒስቴር ከፍተኛ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ አቶ አልቃድር አህመድ እንደገለጹት፤ በየአካባቢው ያሉ የቱሪዝም መዳረሻ ስፍራዎችን የማልማትና የማስተዋወቅ ስራ በትኩረት እየተከናወነ ይገኛል።ጉብኝቱም የዚሁ ጥረት አካል ነው ብለዋል።   የጉብኝቱ ተሳታፊዎች ከቤተ መንግስት በተጨማሪ ተራራ የመውጣት ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም የስፖርት ቱሪዝምን ጨምሮ ሌሎች አማራጮችን በመጠቀም በየአካባቢው ያሉ የቱሪዝም መዳረሻ ስፍራዎችን የማስተዋወቅ ስራ እንደሚጠናከር ገልጸዋል። የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የኮሙኒኬሽን ሀላፊ ሃና ገብረስላሴ በበኩላቸው፤ ታላቁ ሩጫ በአገራችን ያለውን የቱሪዝም ጸጋ በማስተዋወቅ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ብለዋል።   በዛሬው እለትም መነሻውን ከደብረ ብርሃን ከተማ ዘርዓያቆብ አደባባይ እስከ አንኮበር ቤተመንግስት የ42 ኪሎ ሜትር ጉዞ በማድረግ ጉብኝት ማካሄዳቸውን ተናግረዋል። በነገው እለትም "ከአንኮበር እስከ ሀረር በር" በሚል መሪ ሃሳብ በስድስት የክልል ከተሞች የሚካሄደው የታላቁ ሩጫ የመጀመሪያ ዙር ሩጫ ውድድር በደብረ ብርሃን ከተማ ይካሄዳል ብለዋል።   በሰሜን ሸዋ ዞን የአንኮበር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ይስማ ተክለፃዲቅ እንዳሉት፤ ወረዳው የቀደምት ነገስታት አብያተ መንግስታትና አስደናቂ መልክአ ምድር ያለው በመሆኑ ለጎብኚዎች ተመራጭ ነው። ከደብረ ብርሃን እስከ አዋሽ አርባ የሚወስደው የአስፋልት መንገድ መገንባቱ የአካባቢውን የቱሪዝም እንቅስቃሴ ለማነቃቃት ትልቅ ድርሻ ያለው መሆኑንም አስረድተዋል።
አዘጋጇ ሞሮኮ ካሜሮንን በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች
Jan 10, 2026 74
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሁለተኛ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ሞሮኮ ካሜሮንን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ብራሂም ዲያዝ በ26ኛው እና ኢስማኤል ሳይባሪ በ74ኛው ደቂቃ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዲያዝ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ አምስት ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነት አጠናክሯል። የሪያል ማድሪዱ የክንፍ መስመር ተጫዋች በአምስት ጨዋታዎች አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። በጨዋታው ሞሮኮ ከፍተኛ ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ካሜሮን ኳስን መስርታ ለመጫወት ተቸግራለች። ግልጽ የግብ እድሎችንም መፍጠር አልቻለችም። ጨዋታውን 64 ሺህ 178 ተመልካቾች ተከታትለውታል። ውጤቱን ተከትሎ ሞሮኮ ግማሽ ፍጻሜ የገባች ሁለተኛ ሀገር ሆናለች። በግማሽ ፍጻሜው ከአልጄሪያ እና ናይጄሪያ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ሞሮኮ ለሁለት ዓመት ገደማ ሽንፈት ባለማስተናገድ በአስደናቂ ግስጋሴ ላይ ትገኛለች። ዛሬ በተደረገው የመጀመሪያ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ ሴኔጋል ማሊን 1 ለ 0 በማሸነፍ የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብታለች። የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ነገም ቀጥሎ ሲውል አልጄሪያ ከናይጄሪያ፣ ኮትዲቯር ከግብጽ ጋር ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ተጠባቂው የፋሲል ከነማ እና ኢትዮጵያ ቡና ጨዋታ
Jan 10, 2026 67
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ዛሬ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ፋሲል ከነማ ከኢትዮጵያ ቡና በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ፋሲል ከነማ በሊጉ ባደረጋቸው 13 ጨዋታዎች ስድስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሰባት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በ13ቱ ጨዋታዎች 10 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ሶስት ጎሎች ተቆጥረውበታል። በ25 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ፋሲል ከነማ በዘንድሮው የውድድር ዓመት ሽንፈት ያላስተናገደ ብቸኛው ክለብ ነው። በሊጉ አንስተኛ የግብ መጠን የተቆጠረበትም ቡድን ነው። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና በሊጉ 13 ጨዋታዎች አከናውኖ በአራቱ አሸንፎ በስድስቱ ሲሸነፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 11 ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎችን አስተናግዷል። ኢትዮጵያ ቡና በ15 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ጨዋታው ሁለቱ ክለቦች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። ፋሲል ከነማ ካሸነፈ ወደ ነበረበት ሁለተኛ ደረጃ ይመለሳል። በሌላኛው መርሃ ግብር ወላይታ ድቻ ከኢትዮጵያ መድን ምሽት 12 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወላይታ ድቻ እስከ አሁን በሊጉ ማሸነፍ የቻለው ጨዋታ ብዛት ሁለት ብቻ ነው። አምስት ጊዜ ሲሸነፍ ስድስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 13 ግቦችን ሲያስቆጥር 16 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን 13 ጨዋታዎችን አድርጎ ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ስድስት ጊዜ ተሸንፏል። በአራቱ ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 14 ግቦችን ተቆጥረውበታል። ኢትዮጵያ መድን በ13 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። መቻል ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቻል በ20 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ባህር ዳር ከተማ በ16 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በሌላኛው መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሀድያ ሆሳዕና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ16 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ሀድያ ሆሳዕና በተመሳሳይ 16 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ኢትዮጵያ የምትሳተፍበት 46ኛው የዓለም አትሌቲክስ የሀገር አቋራጭ ሻምፒዮና ዛሬ ይካሄዳል
Jan 10, 2026 85
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ 46ኛው የዓለም አትሌቲክስ የሀገር አቋራጭ ሻምፒዮና ዛሬ በአሜሪካ ታላሃስ ፍሎሪዳ ይደረጋል። በሻምፒዮናው ላይ ከ52 ሀገራት የተወጣጡ 485 አትሌቶች እንደሚሳተፉ የዓለም አትሌቲክስ አስታውቋል። ኢትዮጵያም 20 አትሌቶችን በተለያዩ ርቀቶች ታሳትፋለች። 10 ኪሎ ሜትር አዋቂ ወንዶች፣ 10 ኪሎ ሜትር አዋቂ ሴቶች፣ ከ20 ዓመት በታች ወንዶች 8 ኪሎ ሜትር፣ ከ20 ዓመት በታች ሴቶች 6 ኪሎ ሜትር እና ድብልቅ ሪሌይ (4 በ 2 ኪሎ ሜትር) ኢትዮጵያ የምትሳተፍባቸው ርቀቶች ናቸው። በሪሁ አረጋዊ፣ ቢኒያም መሃሪ፣ በረከት ነጋ፣ መዝገቡ ስሜ፣ ንብረት ክንዴ እና ታደሰ ወርቁ በ10 ኪሎ ሜትር አዋቂ ወንዶች የሚሳተፉ አትሌቶች ናቸው። በ10 ኪሎ ሜትር ሴቶች አሳየች አይቼው፣ አለሺኝ ባወቀ፣ ሹሬ ደምሴ፣ ሰናይት ጌታቸው፣ ለምለም ንብረት እና ዓለም ንጉስ ኢትዮጵያን ወክለው ይወዳደራሉ። ከ20 ዓመት በታች ወንዶች 8 ኪሎ ሜትር አየለ ሰውነት ይሳተፋል። ማርታ አለማየሁ፣ ወሰኔ አሰፋ እና የኔነሽ ሽመክት ከ20 ዓመት በታች ሴቶች 6 ኪሎ ሜትር የሚሳተፉ አትሌቶች ናቸው።   በድብልቅ ሪሌይ ሂሩት መሻሻ እና ገላ ሀምበሴ እንዲሁም ሚልኬሳ ፍቃዱ እና ወገኔ አዲሱ (ወንድ) ይሳተፋሉ። የኢትዮጵያ አትሌቶች ለውድድሩ ለ47 ቀናት ዝግጅት ማድረጋቸውን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። አትሌቶቹ የተመረጡት በጥቅምት ወር 2018 ዓ.ም በተካሄደው 43ኛው ጃንሜዳ ኢንተርናሽናል አገር አቋራጭ ውድድር ባስመዘገቡት የተሻለ ውጤት ነው። በውድድሩ ላይ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልዑካን ቡድን በሳምንቱ አጋማሽ ወደ ፍሎሪዳ ማምራቱ ይታወቃል። ከዛ አስቀድሞ በሀገር ቤት ሽኝት ተደርጎለታል። የዛሬ ውድድሮች በኢትዮጵያ ሰዓት አቆጣጠር ከቀኑ 11 ሰዓት ከ45 አንስቶ ይካሄዳሉ። የኢትዮጵያ፣ ኬንያ እና ዩጋንዳ አትሌቶች ውድድሩን የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት አግኝተዋል። የአሜሪካ፣ ፈረንሳይ፣ ስፔን፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ አውስትራሊያ እና ጃፓን አትሌቶች ጠንካራ ተፎካካሪ ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል። በአዋቂ ወንዶች እና ሴቶች የ10 ኪሎ ሜትር የሚያሸንፉ አትሌቶች በተመሳሳይ የ30 ሺህ የአሜሪካን ዶላር ሽልማት ያገኛሉ። በሁለቱም ጾታዎች የአዋቂ ውድድሮች አጠቃላይ የሚያሸንፉ ቡድኖች እያንዳንዳቸው ቡድኖች የ20 ሺህ የአሜሪካን ዶላር ሽልማት ይበረከትላቸዋል። በድብልቅ ሪሌይ የሚያሸንፈው ሀገር 12 ሺህ የአሜሪካን ዶላር እንደሚያገኝ የዓለም አትሌቲክስ መረጃ ያመለክታል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2024 በሰርቢያ ቤልግሬድ በተካሄደው 45ኛው የዓለም አትሌቲክስ የሀገር አቋራጭ ሻምፒዮና ሁለት የወርቅ፣ ስድስት የብር እና ሁለት የነሐስ በድምሩ 10 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ኬንያን ተከትላ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቋ የሚታወስ ነው። ኢትዮጵያ በሻምፒዮና ተሳትፎ ታሪኳ 109 የወርቅ፣ 121 ብር እና 65 የነሐስ በድምሩ 295 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ከኬንያ በመቀጠል ስኬታማዋ ሀገር ናት። ኬንያ 157 ወርቅ፣ 110 የብር እና 78 የነሐስ በድምሩ 345 ሜዳሊያዎችን በማግኘት የበላይነቱን ይዛለች።
የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ከግብጽ የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል
Jan 10, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቀሪ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ግብጽ ከኮትዲቯር በአጋዲር ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ግብጽ ቤኒንን፣ ኮትዲቯር ቡርኪናፋሶን በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅለዋል። ከዚህ ቀደም ሀገራቱ በአፍሪካ ዋንጫው አራት ጊዜ ተገናኝተዋል። ግብጽ እ.እ.አ. በ2006 ባዘጋጀችው 32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በፍጻሜው ኮትዲቯር ጋር በፍጻሜው ተገናኝታ በመለያ ምት 4 ለ 2 በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ቡድኖቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተገናኙት ሱዳን እ.አ.አ በ1970 ባዘጋጀችው ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። ሶስተኛ ደረጃን ለመያዝ ባደረጉት ጨዋታ ግብጽ 3 ለ 1 በማሸነፍ ሶስተኛ ሆና አጠናቃለች። ግብጽ ከኮትዲቯር ጋር በአፍሪካ ዋንጫ ያደረገቻቸውን አራት ጨዋታዎች አሸንፋለች። በዘንድሮው አፍሪካ በጥሩ ብቃት ላይ የሚገኙት ሀገራት ጠንካራ ፍልሚያ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። መሐመድ ሳላህ እና ኦማር ማርሙሽ ከግብጽ፣ አማድ ዲያሎ እና ፍራንክ ኬሲዬ ከኮትዲቯር በጨዋታው ላይ ልዩነት ይፈጥራሉ ተብለው ግምት ያገኙ ተጫዋቾች ናቸው። ኮትዲቯር የአፍሪካ ዋንጫ ክብሯን ለማስጠበቅ የሰባት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋን ግብጽን ማሸነፍ ይጠበቅባታል። የሁለቱ ሀገራት አሸናፊ በግማሽ ፍጻሜው ከሴኔጋል ጋር ይጫወታል። በሌላኛው የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር አልጄሪያ ከናይጄሪያ ምሽት አንድ ሰዓት ላይ በማራካሽ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።   በጥሎ ማለፉ አልጄሪያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን፣ ናይጄሪያ ሞዛምቢክን በማሸነፍ ስምንት ውስጥ ገብተዋል። ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለ10ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ዘጠኝ ጨዋታዎች አልጄሪያ አራት ጊዜ ስታሸንፍ ናይጄሪያ ሶስት ጊዜ ድል ቀንቷታል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ከዘጠኙ ጨዋታዎች መካከል ሁለቱ በፍጻሜ የተገናኙባቸው ናቸው። ናይጄሪያ እ.አ.አ በ1980 ባዘጋጀችው 12ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በፍጻሜው አልጄሪያን 3 ለ 0 በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ፓትሪክ ኦሊሴጉን ኦዴግባሚ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሙዳሺሩ ባባቱንዴ ላዋል ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ በ1990 በአልጄሪያ በተካሄደው 17ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጇ ሀገር በፍጻሜው ናይጄሪያን በቼሪፍ ኡጃኒ ግብ 1 ለ 0 በመርታት ዋንጫውን ከፍ አድርጋለች። ሀገራቱ ለመጨረሻ ጊዜ በአህጉራዊው መድረክ የተገናኙት እ.አ.አ 2019 ግብጽ ባዘጋጀችው 32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በግማሽ ፍጻሜው ሲሆን አልጄሪያ 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜው አልፋለች። አልጄሪያ በፍጻሜው ሴኔጋልን በማሸነፍ ለሁለተኛ ጊዜ ዋንጫውን አንስታለች። በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ያደረጓቸውን ጨዋታዎች በሙሉ ያሸነፉት ሁለቱ ሀገራት በዛሬው መርሃ ግብር ጠንካራ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። የጨዋታው አሸናፊ በግማሽ ፍጻሜው ከሞሮኮ ጋር ይገናኛል። ትናንት በተደረጉ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ሴኔጋል እና አዘጋጇ ሞሮኮ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል።
ሴኔጋል ለግማሽ ፍጻሜ ያለፈች የመጀመሪያዋ ሀገር ሆነች
Jan 9, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ጥር 1/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ሴኔጋል ማሊን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በታንጀር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኢሊማን ንጃይ በ27ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። የማሊው አምበል ይቪስ ቢሱማ በሁለት ቢጫ በመጀመሪያው አጋማሽ ማብቂያ ላይ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ይህም ማሊን በሁለተኛው አጋማሽ በ10 ተጫዋች እንድትጨርስ አስገድዷታል። ማሊ በውድድሩ በአጠቃላይ ሶስተኛ ቀይ ካርድ ያገኘች ሲሆን በዚህም ከፍተኛውን ቀይ ካርድ የተመለከተች ሀገር ሆናለች። ከቀይ ካርዱ በፊት በጨዋታው ብልጫ ወስዳ የተጫወተችው ሴኔጋል የቁጥር ብልጫው ጨዋታውን የበለጠ እንድትቆጣጠር አስችሏታል። ውጤቱን ተከትሎ ሴኔጋል ግማሽ ፍጻሜውን የተቀላቀለች የመጀመሪያ ሀገር ሆናለች። በግማሽ ፍጻሜው ከኮትዲቯር እና ግብጽ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ካሜሮን ከአዘጋጇ ሞሮኮ ጋር በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
በተጠባቂው ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን አሸነፈ 
Jan 9, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ጥር 1/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 14ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሃዋሳ ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን 1 ለ 0 አሸንፏል። ሃዋሳ ከተማ ከቅዱስ ጊዮርጊስ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው አማድ ዲያሎ - የአፍሪካ እግር ኳስ ብሩህ ተስፋ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሽመልስ በቀለ በ46ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ከሁለት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሃዋሳ ከተማ በ24 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ19 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል።ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።   በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሃ ግብር ድሬዳዋ ከተማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ መቀሌ 70 እንደርታ ከሸገር ከተማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ።
አማድ ዲያሎ - የአፍሪካ እግር ኳስ  ብሩህ ተስፋ
Jan 9, 2026 185
ተጫዋቹ አዲሱ ሳሙኤል ኤቶ የሚል ስያሜ እየተሰጠው ይገኛል። ፍጥነቱን ከዲዲየር ድሮግባ ጋር ያነጻጽሩታል። ለተጋጣሚ ተጫዋቾች የራስ ምታት እና ፈተና የሆነውን ግራ እግሩን ከሌላኛው የግራ እግር ምትሃተኛ ሪያድ ማህሬዝ ጋር የሚያወዳድሩም አልጠፉም።   በዚህ አካሄዱ ከቀጠለ ያለ ምንም ጥርጥር ወደፊት በእግር ኳስ ከምንመለከታቸው ኮከቦች አንዱ ሊሆን ይችላል እየተባለለት ይገኛል። ይህ ተጫዋች በማንችስተር ዩናይትድ የ147 ዓመታት ታሪክ ሀትሪክ የሰራ የመጀመሪያው አፍሪካዊ ተጫዋች ነው። እያወራን የምንገኘው የማንችስተር ዩናይትድ 16 ቁጥር ማልያ ለባሽ አማድ ዲያሎ ነው። የ23 ዓመቱ ኮትዲቯራዊ ተስፈኛ ተጫዋች በቀያዮቹ ሴጣኖች እያሳየ ያለው ብቃት ከብዙዎች ዘንድ ሙገሳ አስችሮታል፣ አድናቆት እንዲጎርፍለት አድርጓል። ወደ ኋላ መለስ እንበልና የአማድ ዲያሎን መነሻ እንመልከት። ካሜሮን ከአዘጋጇ ሞሮኮ ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው አማድ የተወለደው እ.አ.አ ጁላይ 11 2002 በኮትዲቭዋር መዲና አቢጃን ነው። ተጫዋቹ በአፍሪካ ምድር ቢወለድም ገና በህጻንነት እድሜው ነበር ወደ ጣልያን የተሰደደው። የእግር ኳስ ህይወቱን የጀመረው እ.አ.አ በ2014 በጣልያን ሬጂዮ ኢሚሊያ ግዛት በሚገኘው ቦካ ባርኮ የታዳጊ ቡድን ነው። ቡድኑን በተቀላቀለበት ዓመት የገና በዓል (ክሪስማስን) በማስመልከት በተካሄደ ውድድር ላይ በ12 ዓመቱ ኮከብ ግብ አግቢ ሲሆን ያሳየው አስደማሚ ብቃት የብዙዎችን ቀልብ ሳበ። ይህ የገና በዓል ውድድር አማድን እ.አ.አ በ2015 በቦካ ባርኮ ቡድን እንዲመዘገብ አደረገው። ተጫዋቹ በቡድኑ ብዙም አልቆየም። የበርካታ የጣልያን ሴሪአ ክለቦች አይን አረፈበት። ብዙም ሳይቆይ በዛው በ2015 ወደ ጣልያኑ አትላንታ አመራ።   አማድ ከእ.አ.አ 2015 እስከ 2019 ለአትላንታ ታዳጊ ቡድን የተጫወተ ሲሆን እ.አ.አ 2019 እና 20 ለዋናው ቡድን ተጫውቷል። ለዋናው ቡድን አራት ጨዋታዎችን አድርጎ ማስቆጠር የቻለው አንድ ግብ ብቻ ነው። የእንግሊዙ ክለብ ማንችስተር ዩናይትድ ተጫዋቹ በጣልያኑ ክለብ ባሳየው ብቃት በ18 ዓመት እድሜው እ.አ.አ ጃንዋሪ ወር 2021 በአምስት ዓመት ኮንትራት በ37 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዩሮ አስፈርሞታል። ተጫዋቹ ወደ ማንችተር ሲመጣ ቀጥታ ወደ ዋናው ቡድኑ አልተቀላቀለም። በቡድኑ ከ23 ዓመት በታች ጨዋታውን ማድረግ ጀመረ። አማድ የመጀመሪያ ጨዋታውን ለማንችስተር ያደረገው እ.አ.አ ፌብሩዋሪ 18 2021 ቡድኑ ከሪያል ሶሲዬዳድ ጋር ባደረገው የዩሮፓ ሊግ ጨዋታ ነው። በዛው ዓመት በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ እና አውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ዲያሎ ከእ.አ.አ 2022-2023 ባለው ጊዜ ሬንጀርስ እና ሰንደርላንድ በውሰት የተጫወተ ሲሆን በቡድኖቹ ባደረጋቸው 47 ጨዋታዎች 16 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል።   እ.አ.አ በ2023/24 አማድ ወደ ማንችስተር ዩናይትድ በመመለስ በድጋሚ መጫወት ጀምሯል። በክለቡም ድንቅ ብቃቱን እያሳየ መምጣት ጀመረ። እ.አ.አ ጥር 17 2025 ማንችስተር ዩናይትድ ከሊጉ ከወረደው ሳውዝሃምፐን ጋር በነበረው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መርሃ ግብር በ12 ደቂቃ ውስጥ ሶስት ግቦችን አስቆጥሮ ሀትሪክ በመስራት ቡድኑ 3 ለ 1 አንዲያሸንፍ ያደረገበት መንገድ አድናቆት አስችሮታል። በዚህም አማድ በማንችስተር ዩናይትድ የ147 ታሪክ የመጀመሪያ ሀትሪክ የሰራ አፍሪካ ተጫዋች በመሆን አዲስ ታሪክ ጽፏል። አማድ በቀያዮቹ ሴጣኖች ማልያ እስከ አሁን ባደረጋቸው 53 ጨዋታዎች 11 ግቦችን አስቆጥሯል። ተጫዋቹ ከክለቡ በተጨማሪ ለኮትዲቯር ብሄራዊ ቡድን በመጫወት ላይ ይገኛል። እ.አ.አ 2021 ኮትዲቯር ከኒጀር ጋር ባደረገችው ጨዋታ በ86ኛው ደቂቃ ተቀይሮ በመግባት ለብሄራዊ ቡድኑ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ለሀገሩ እስከ አሁን ባደረጋቸው 15 ጨዋታዎች አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። የመጀመሪያ ጎሉን ኮትዲቯር በ2021 በወዳጅነት ጨዋታ ቡርኪናፋሶን 2 ለ 1 ስታሸነፍ ነበር ያስቆጠረው። አማድ ዲያሎ ዘንድሮ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ድንቅ ጊዜ እያሳለፈ ይገኛል። አማድ በውድድሩ ላይ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሶስት ግቦችን ያስቆጠረ ሲሆን አንድ ለግብ የሚሆን ግብ አመቻችቶ አቀብሏል። ኮትዲቯር ከሞዛምቢክ፣ ካሜሮን እና ቡርኪናፋሶ ጋር ባደረገቻቸው ጨዋታዎች የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተምርጧል። የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ሩብ ፍጻሜ እንድትደርስ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል። ኮትዲቯር ከግብጽ በሩብ ፍጻሜው ነገ ከግብጽ ጋር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በአጋዲር ስታዲየም የምታደርገው ጨዋታ በጉጉጉት ይጠበቃል። ሀገሩ በጠዋታው ላይ ከአማድ ብዙ ትጠብቃለች። ወደ ክለብ እንቅስቃሴው ስንመለስ አማድ በማንችስተር ዩናይትድ ስብስብ ውስጥ ቁልፍ የሚባል ተጫዋች ነው። ፈጣን ኳስን የማንከበላል ክህሎቱ፣ ፍጥነቱ ፣ የቴክኒክ አቅሙ፣ ጨዋታን የማንበብ ብቃቱ እና ሁለቱንም እግሩን የመጠቀም አቅሙ አልፎም ተጫዋቾችን በቄንጥ የሚያልፍበት መንገድ ተጫዋቹን እያስወደሰው ነው። አማድ ዲያሎ ከክንፍ ተጫዋችነቱ ባሻገር የአጥቂ አማካይ ሆኖ መጫወትም ይችላል። እ.አ.አ በ2020 የ18 ዓመት ልደቱን ተከትሎ ተጫዋቹ ስሙን ከአማድ ትራኦሬ ወደ አማድ ዲያሎ አስቀይሯል። አማድ ካለው ድንቅ ብቃት አንጻር ወደፊት በክለብ እና ብሄራዊ ቡድን ደረጃ ድንቅ ጊዜን ካሳለፉ ታዋቂ የአፍሪካ ተጫዋቾች ተርታ የመሰለፉ ጉዳይ አያጠራጥርም።
ሃዋሳ ከተማ ከቅዱስ ጊዮርጊስ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው 
Jan 9, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ጥር 1/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 14ኛ ሳምንት ዛሬም ቀጥሎ ሲውል ሶስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ሃዋሳ ከተማ ከቅዱስ ጊዮርጊስ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። የሁለት ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ሃዋሳ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 13 ጨዋታዎች ስድስት ጊዜ ሲያሸንፍ በአራቱ ተሸንፏል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። በ13ቱ ጨዋታዎች 14 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 10 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ21 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ 13 ጨዋታዎችን አከናውኖ በአምስቱ ድል ሲቀናው አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በአምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 11 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ዘጠኝ ግቦችን አስተናግዷል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በ19 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሃዋሳ ከተማ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ቅዱስ ጊዮርስ ከአምስት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በሌላኛው መርሃ ግብር ድሬዳዋ ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ድሬዳዋ ከተማ በ17 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ21 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። መቀሌ 70 እንደርታ ከሸገር ከተማ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። መቀሌ 70 እንደርታ በ11 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሸገር ከተማ በ13 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በጨዋታው መቀሌ 70 እንደርታ ካሸነፈ ከወራጅ ቀጠና ይወጣል። ሸገር ከተማ ከአራት ተከታታይ የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል።
ካሜሮን ከአዘጋጇ ሞሮኮ ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 9, 2026 141
አዲስ አበባ፤ ጥር 1/2018 (ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከሁለት ቀናት እረፍት በኋላ ዛሬ በሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ይመለሳል። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ካሜሮን ከሞሮኮ በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ የእግር ኳስ አፍቃሪያንን ትኩረት ስቧል። በጥሎ ማለፉ ካሜሮን ደቡብ አፍሪካን፣ ሞሮኮ ታንዛንያን በማሸነፍ የመጨረሻ ስምንት ውስጥ ገብተዋል። ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። ግብጽ እ.አ.አ በ1986 ባዘጋጀችው 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሁለት ተገናኝተው አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሮጀር ሚላ ለካሜሮን፣ አብዱልከሪም ሜሪ ለሞሮኮ በወቅቱ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። እ.አ.አ በ1988 በሞሮኮ በተካሄደው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በግማሽ ፍጻሜው ተጫውተው ካሜሮን በስሪል ቶማስ ማካናኪ ግብ 1 ለ 0 በማሸነፍ ለፍጻሜው አልፋለች። ካሜሮን በፍጻሜው ናይጄሪያን በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ሴኔጋል እ.አ.አ በ1992 ባዘጋጀችው 18ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሁለት ተገናኝተው ካሜሮን በአንድሬ ካና-ቢይክ 1 ለ 0 አሸንፋለች። በአጠቃላይ ሁለቱ ቡድኖች በአህጉራዊው መድረክ ሶስት ጊዜ ተገናኝተው ካሜሮን ሁለት ጊዜ ስታሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። ሁለቱ ሀገራት ከ34 ዓመታት በኋላ ዳግም በአፍሪካ ዋንጫ ተገናኝተዋል። አምስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን በማንሳት ከግብጽ ቀጥሎ ስኬታማ የሆነችው ካሜሮን እና የአፍሪካ የወቅቱ ምርጥ ቡድን ተብላ የተሰየመችው ሞሮኮ የሚያደርጉት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። አዘጋጇ ሞሮኮ የአፍሪካ ዋንጫን አንድ ጊዜ አንስታለች። የሁለቱ ቡድኖች አሸናፊ ከናይጄሪያ እና አልጄሪያ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። በሌላኛው የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ማሊ ከሴኔጋል ምሽት አንድ ሰዓት ላይ በታንጀር ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በጥሎ ማለፉ ማሊ ቱኒዚያን፣ ሴኔጋል ሱዳንን በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅለዋል። ሀገራቱ በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። ቱኒዚያ እ.አ.አ በ2004 ባዘጋጀችው 24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሁለት ተጫውተው አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሃቢብ ፍሬድሪክ ቤይ ለሴኔጋል፣ ድራማኔ ትራኦሬ ለማሊ በወቅቱ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። ከ22 ዓመታት በኋላ በአፍሪካ ዋንጫው ወደ ግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ በሚደረግ ፍልሚያ ይገናኛሉ። ማሊ በአፍሪካ ዋንጫ ትልቅ ውጤቷ በስምንተኛው እና በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችበት ነው። ሴኔጋል አንድ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አንስታለች። በኮከብ ተጫዋቾች ስብስብ የተሞላችው ሴኔጋል የማሸነፍ ቅድሚያ ግምቱን አግኝታለች። አንድም ጨዋታ ሳታሸንፍ ሩብ ፍጻሜ የደረሰችው ማሊ ለተጋጣሚዋ ጠንካራ ፈተና ትሆናለች ተብሎ ይጠበቃል። የማሊ እና ሴኔጋል አሸናፊ በግማሽ ፍጻሜው ከግብጽ እና ኮትዲቯር አሸናፊ ጋር ይጫወታል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም