ቀጥታ፡
ስፖርት
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ከዛምቢያ ጋር ይጫወታል
May 31, 2026 240
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ ኢትዮጵያ የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ ጨዋታዋን ከዛምቢያ ጋር ታደርጋለች። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ትናንት በሁለተኛ ዙር የመልስ ጨዋታ ብሩንዲን 2 ለ 1 በማሸነፍ በድምሩ ተጋጣሚውን 4 ለ 2 በመርታት ለመጨረሻው ዙር ማጣሪያ አልፏል። በአሰልጣኝ ራውዳ አሊ የሚመራው ብሔራዊ ቡድን የመጨረሻ ዙር ጨዋታውን ከዛምቢያ ጋር እንደሚያደርግ ታውቋል። የዛምቢያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዛሬ ከሜዳው ውጪ ባደረገው የመልስ ጨዋታ 2 ለ 0 አሸንፏል። በኪባሳ ማሊባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፒዳህ ሙዙዋ እና ኤልሳቤት ሞፍያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ዛምቢያ በድምር ውጤት 7 ለ 0 በማሸነፍ የመጨረሻውን ዙር ተቀላቅላለች። ዛምቢያ ከኢትዮጵያ ጋር ለዓለም ዋንጫው ለማለፍ ትጫወታለች። ኢትዮጵያ ከዛምቢያ ጋር የዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎቿን በሰኔ ወር መጨረሻ እና ሐምሌ ወር መጀመሪያ ላይ ታደርጋለች። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። ቀሪ አራት ሀገራት በማጣሪያ ጨዋታዎች ይለያሉ።
ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ የካራቴ ሻምፒዮና አራት የወርቅ ሜዳሊያዎችን አገኘች
May 31, 2026 331
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የካራቴ ሻምፒዮና ከግንቦት 20 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በኬንያ ናይሮቢ እየተካሄደ ይገኛል። በሻምፒዮና ላይ እየተሳተፈ የሚገኘው የኢትዮጵያ ካራቴ ብሔራዊ ቡድን እስከ አሁን ዘጠኝ ሜዳሊያዎችን አግኝቷል። ብሔራዊ ቡድኑ በወንዶች ከ75 ኪሎ ግራም በታች እና ከ53 ኪሎ ግራም በታች፣ እንዲሁም በሴቶች ካታ እና በቡድን የካራቴ ኩሚቴ አራት የወርቅ ሜዳሊያዎችን ማግኘት ችሏል። በተጨማሪም በወንዶች ከ67 ኪሎ ግራም በታች እና በቡድን ካታ ውድድር ሁለት የብር ሜዳሊያዎች ተገኝተዋል። በወንዶች ካታ፣ ከ60 ኪሎ ግራም በታች እና ከ84 ኪሎ ግራም በታች ሶስት የነሐስ ሜዳሊያዎች የተመዘገበባቸው ሌሎች ዘርፎች ናቸው። የምስራቅ አፍሪካ የካራቴ ሻምፒዮና ውድድር ዛሬ ፍጻሜውን የሚያገኝ ሲሆን አምስት አገራት መሳተፋቸውን የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታውቋል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2025 በአዲስ አበባ በተካሄደው የምስራቅ አፍሪካ የካራቴ ሻምፒዮና አጠቃላይ አሸናፊ እንደነበረች የሚታወስ ነው።
ፒኤስጂ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫን ለተከታታይ ጊዜ አነሳ
May 30, 2026 962
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ ፒኤስጂ አርሰናልን በመለያ ምት አሸንፏል። ማምሻውን በሀንጋሪ ቡዳፔስት በሚገኘው ፑሽካሽ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ካይ ሃቫርትዝ በስድስተኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል አርሰናል መሪ ሆኗል። የፒኤስጂው አምበል ማርኪኒዮስ ስህተት ለሃቫርትዝ ግብ መቆጠር ምክንያት ሆኗል። ከእረፍት መልስ ኡስማን ዴምቤሌ በ65ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ ባሳረፈው ጎል ፒኤስጂ አቻ መሆን ችሏል። የወቅቱ የባለንዶር አሸናፊ ዴምቤሌ ዘንድሮ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ስምንት አድርሷል። መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት በመጠናቀቁ ምክንያት 30 ደቂቃ ተጨምሯል። በጭማሪ ሰዓት ግብ ባለመቆጠሩ ምክንያት ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቷል። ፒኤስጂ በመለያ ምት 4 ለ 3 በማሸነፍ ለተከታታይ የውድድር ዓመት የሻምፒዮንስ ሊጉን ዋንጫ አንስቷል። የአውሮፓ ክብሩን አስጠብቋል። የፓሪሱ ክለብ ከሪያል ማድሪድ በኋላ ለተከታታይ ዓመት ዋንጫውን ያነሳ ቡድን ሆኗል። የሰሜን ለንደኑ ክለብ አርሰናል ለመጀመሪያ ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የማንሳት ህልሙ አልተሳካም። አርሰናል ከፕሪሚየር ሊጉ ድል በኋላ ድርብ ስኬት ማሳካት አልቻለም።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገዋል
May 30, 2026 600
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ጨዋታዎች ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮጵያ መድን እና መቀሌ 70 እንደርታ ከባህር ዳር ከተማ ነጥብ ተጋርተዋል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ ተለያይተዋል። የወልዋሎው ጌቱ ኃይለማርያም በሰባተኛው ደቂቃ በራሱ መረብ ላይ ያስቆጠረው ግብ ኢትዮጵያ መድንን መሪ ሆኗል። የኢትዮጵያ መድኑ ጋናዊ ተጫዋች እስማኤል አብዱልጋኒዩ በ12ኛው ደቂቃ በራሱ ላይ ባስቆጠረው ግብ ወልዋሎ አቻ መሆን ችሏል። ውጤቱን ተከትሎ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ41 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ43 ነጥብ ደረጃውን ከ13ኛ ወደ 12ኛ ከፍ አድርጓል። መድን ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ባህር ዳር ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። መቀሌ 70 እንደርታ በ35 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው ባህር ዳር ከተማ በበኩሉ በ46 ነጥብ ከነበረበት 9ኛ ደረጃ ወደ 6ኛ ከፍ ብሏል። ‘ ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በበርካታ ጨዋታዎች አቻ የወጣ (19 ጊዜ) ቡድን ነው። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ሲዳማ ቡና አዳማ ከተማን 1 ለ 0 በማሸነፍ መሪነቱን አጠናክሯል። በዝናብ ምክንያት ዛሬ ከቆመበት ቀጥሎ በተካሄደው ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ተጠናቋል። ፕሪሚየር ሊጉ ኢትዮጵያ ከማላዊ ጋር በምታደርጋቸው የወዳጅነት ጨዋታዎች ምክንያት የሚቋረጥ ሲሆን፣ ሰኔ 7 ቀን 2018 ዓ.ም በ35ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ይመለሳል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ወደ ዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ አለፈ
May 30, 2026 577
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ኢትዮጵያ ብሩንዲን 2 ለ 1 አሸንፋለች። በኢንትዋሪ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳንሲል ኢራንዚ በስምንተኛው ደቂቃ ባስቆጠረችው ጎል ብሩንዲን መሪ ሆናለች። ምኅረት አየለ በ53ኛው እና ሊዲያ እያሱ በ73ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፏቸው ግቦች ኢትዮጵያን አሸናፊ አድርገዋል። ሊዲያ እያሱ በመጀመሪያው ጨዋታ ሁለት ግቦችን ማስቆጠሯ የሚታወስ ነው። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ በድምር ውጤት ብሩንዲን 4 ለ 2 በማሸነፍ ወደ ዓለም ዋንጫው የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ አልፋለች። ኢትዮጵያ በመጨረሻው ዙር ከዛምቢያ እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች በመጀመሪያ ዙር ባደረጉት ጨዋታ ዛምቢያ 5 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፋለች። የሀገራቱ የመልስ ጨዋታ ነገ ይደረጋል። ኢትዮጵያ የዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎችን በሰኔ ወር መጨረሻ እና ሐምሌ ወር መጀመሪያ ላይ ታደርጋለች። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። ቀሪ አራት ሀገራት በማጣሪያ ጨዋታዎች ይለያሉ።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድል ቀንቶታል
May 30, 2026 212
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ናትናኤል ዳንኤል የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። ሀብታሙ ሸዋለም የኢትዮ ኤሌክትሪክን ብቸኛ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ45 ነጥብ ደረጃውን ከ14ኛ ወደ 9ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ46 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ ናትናኤል ዳንኤል በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ቁጥር 13 በማድረስ፣ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን ደረጃ በ14 ጎሎች እየመራ ከሚገኘው የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው በአንድ ግብ ብቻ ዝቅ ብሎ በሁለተኛነት ይከተላል። በከባድ ዝናብ ምክንያት ትናንት በአዲስ አበባ ስታዲየም የተቋረጠው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ፣ ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ከቆመበት ቀጥሎ ተካሂዷል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን የመልስ ጨዋታውን ከብሩንዲ ጋር ያደርጋል
May 30, 2026 261
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ ኢትዮጵያ ከብሩንዲ ጋር ዛሬ የመልስ ጨዋታዋን ታከናውናለች። የሀገራቱ ጨዋታ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በኢንትዋሪ ስታዲየም ይካሄዳል። ሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች ግንቦት 16 ቀን 2018 ዓ.ም በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ 2 ለ 1 አሸንፋለች። ሊዲያ እያሱ ግቦቹን ለኢትዮጵያ አስቆጥራለች። አኒታ ንዲኩማና የብሩንዲ ብቸኛ ግብ ከመረብ ላይ አሳርፋለች። በራውዳ አሊ የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን የመልስ ጨዋታውን ለማድረግ ወደ ቡጁምቡራ ግንቦት 19 ቀን 2018 ዓ.ም አምርቷል። ብሔራዊ ቡድኑ ለቀናት ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቶ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት ጨዋታው በሚደረግበት በኢንትዋሪ ስታዲየም አድርጓል። ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት እና የጨዋታ ዝግጁነት ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በፓትሪክ ሳንጋዋ የሚመራው የብሩንዲ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከኢትዮጵያ ጋር ለሚያደርገው የመልስ ጨዋታ ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቷል። ኢትዮጵያ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈች በመጨረሻው ዙር ማጣሪያ ከዛምቢያ እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። ቀሪ አራት ሀገራት በማጣሪያ ጨዋታዎች ይለያሉ።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከአዳማ ከተማ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው
May 30, 2026 175
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ ሰባት ሰዓት ሲዳማ ቡና ከአዳማ ከተማ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሲዳማ ቡና በ58 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። አዳማ ከተማ በ39 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። በ33ኛ ሳምንት አርባምንጭ ከተማን 3 ለ 0 በመርታት ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሲዳማ ቡና ሶስት ነጥብ ማግኘት መሪነቱን ያጠናክርለታል። ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋተታዎች አንዱን በማሸነፍ የመውረድ ስጋት ውስጥ የገባው አዳማ ከተማ በሊጉ ለመቆየት በሚያደርገው ጉዞ ከዛሬው ጨዋታ ሶስት ነጥብ ማግኘት ግድ ይለዋል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሐ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮጵያ መድን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ40 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ መድን በ42 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። በ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከአዳማ ከተማ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ እና ወራጅ ከመሆን ስጋት ለመላቀቅ የሚያደርጉት ፍልሚያ ይጠበቃል። ከቀኑ 10 ሰዓት መቀሌ 70 እንደርታ ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቀሌ 70 እንደርታ በ34 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በ45 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ ሸገር ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። ባህር ዳር ከተማ ደግሞ ከመቻል ጋር አንድ አቻ ተለያይቷል። መቀሌ 70 እንደርታ ሶስት ነጥብ ማግኘት ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ትግል ወሳኝ ነው። ተጋጣሚው ባህር ዳር ከተማ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በበርካታ ጨዋታዎች (18 ጊዜ) አቻ የወጣ ቡድን ነው። በተያያዘም ትናንት በዝናብ ምክንያት የተቋረጠው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጨዋታ ዛሬ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ከ30 በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ከቆመበት ደቂቃ አንስቶ ይቀጥላል። ጨዋታው በአዲስ አበባ ስታዲየም እየተካሄደ በ30ኛው ደቂቃ በከባድ ዝናብ ምክንያት መቋረጡ ይታወቃል። እስከተቋረጠበት ሰዓት በጨዋታው ላይ ምንም ግብ አልተቆጠረም።
ፒኤስጂ እና አርሰናል ለሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ፤ የአምናው አሸናፊ ከታሪክ ፈላጊው ጋር
May 30, 2026 263
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ፒኤስጂ እና አርሰናል ዋንጫውን ለማንሳት የሚያደርጉት ፍልሚያ የዓለም እግር ኳስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። ጨዋታው በሃንጋሪ ቡዳፔስት፣ 67 ሺህ ተመልካቾችን በሚይዘው ፑሽካሽ አሬና ስታዲየም ምሽት አንድ ሰዓት ላይ ይጀምራል። በግማሽ ፍጻሜው ፒኤስጂ ባየር ሙኒክን፣ አርሰናል ደግሞ አትሌቲኮ ማድሪድን በድምር ውጤት በመርታት ለታላቁ የፍጻሜ ጨዋታ ደርሰዋል። ፒኤስጂ በዘንድሮው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ባደረጋቸው 16 ጨዋታዎች ዘጠኙን ሲያሽንፍ በሁለቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 44 ግቦችን ሲያስቆጥር 22 ጎሎች ተቆጥረውበታል። የወቅቱ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የዋንጫ ባለቤት ፒኤስጂ ያስቆጠራቸው ጎሎች ብዛት የማጥቃት አቅሙ ጠንካራ መሆኑን የሚያሳዩ ናቸው። ተጋጣሚው አርሰናል በዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ ምንም ጨዋታ ሳይሸንፍ ለፍጻሜ ደርሷል። ካደረጋቸው 14 ጨዋታዎች መካከል በ11ዱ ድል ሲቀናው በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 29 ግቦችን ሲያስቆጥር ስድስት ጎሎችን ብቻ አስተናግዷል። መድፈኞቹ ከ14ቱ ጨዋታዎች መካከል በዘጠኙ ግብ አለማስተናገዳቸው የተከላካይ መስመር እና አጠቃላይ ጥንካሬ አጉልቶ የሚያሳይ ነው። ሁለቱ ቡድኖች በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሲገናኙ የአሁኑ ለስድስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው አምስት ጨዋታዎች ፒኤስጂ ሁለቱን ሲያሸንፍ አርሰናል አንድ ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በአምስቱ ጨዋታዎች ሁለቱም በተመሳሳይ ስድስት ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝተዋል። ሁለቱ ቡድኖች በውድድሩ የተገናኙት እ.አ.አ በ2024/25 የውድድር ዓመት በግማሽ ፍጻሜ ላይ ነበር። በወቅቱ ፒኤስጂ በድምር ውጤት 3 ለ 1 (1 ለ 0 እና 2 -1) በማሸነፍ ለፍጻሜ ያለፈ ሲሆን በፍጻሜው ኢንተር ሚላንን 5 ለ 0 በመርታት የአውሮፓውን ክብር ለመጀመሪያ ጊዜ ተቀዳጅቷል። ከግማሽ ፍጻሜው በፊት በሊግ ምዕራፍ (League Phase) ተገናኝተው አርሰናል 2 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ፒኤስጂ ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ፍጻሜ ሲደርስ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። የፓሪሱ ክለብ የአውሮፓ ክብሩን ለማስጠበቅ ይጫወታል። አርሰናል ከ20 ዓመታት በኋላ ለፍጻሜው ያለፈ ሲሆን በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫውን ለማንሳት ይፋለማል። መድፈኞቹ ከዚህ ቀደም እ.አ.አ በ2006 ለፍጻሜ ደርሰው በባርሴሎና 2 ለ 1 ተሸንፈው ዋንጫውን ማጣታቸው የሚታወስ ነው። የፒኤስጂው የክንፍ መስመር ተጫዋች ክቪቻ ክቫራትስኬሊያ በዘንድሮው ውድድር 10 ግቦችን ማስቆጠር እና ስድስት ጎሎችን አመቻችቶ በማቀበል የቡድኑ ወሳኝ ተጫዋች መሆኑን አስመስክሯል። ክቫራትስኬሊያ የዓለማችን ምርጡ የክንፍ መስመር ተጫዋች በመባል እየተሞከሸ ይገኛል። የወቅቱ የባለንዶር አሸናፊ ኡስማን ዴምቤሌ ሰባት ግቦችን በማስቆጠር እና ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል ሌላኛው የቡድኑ ቁልፍ ተጫዋች መሆኑን አሳይቷል። በዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ ለአርሰናል በርካታ ግቦችን ያስቆጠረው ጋብርኤል ማርቲኔሊ ነው። ስድስት ግቦችን ከማስቆጠሩም ባለፈ ለሶስት ግቦች መቆጠር ምክንያት ሆኗል። ስዊድናዊው አጥቂ ቪክቶር ዮኮሬሽ አምስት ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ በሁለት ግቦች መቆጠር ላይ ደግሞ አስተዋጽኦ አድርጓል። የተጠቀሱት ተጫዋቾች በጨዋታው ላይ ልዩነት ሊፈጥሩ ይችላሉ ተብሎ ይጠበቃል። ፍልሚያው በማጥቃት አቅሙ በሚታወቀው ፒኤስጂ እና በመከላከል ጥንካሬው በሚደነቀው አርሰናል መካከል የሚደረግ በመሆኑ 'የማጥቃት እና የመከላከል ፍጥጫ' የሚል ስያሜ አግኝቷል። ፒኤስጂ ክብሩን ለማስጠበቅ፣ አርሰናል ለመጀመሪያ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ለመሆን የሚያደርጉት ጨዋታ የዓለምን ትኩረት ስቧል። የ42 ዓመቱ ጀርመናዊ ዳንኤል ሲበርት ተጠባቂውን የፍጻሜ ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
በዝናብ የተቋረጠው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጨዋታ ነገ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም እንዲቀጥል ተወሰነ
May 29, 2026 251
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር በአዲስ አበባ ስታዲየም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና በኢትዮ ኤሌክትሪክ መካከል እየተካሄደ የነበረው ጨዋታ በከባድ ዝናብ ምክንያት ተቋርጧል። ጨዋታው በ34ኛው ደቂቃ ላይ በስታዲየሙ ላይ በጣለው ከባድ ዝናብና ሜዳው ውኃ በመቋጠሩ ምክንያት ሊቋረጥ እንደቻለ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል። ይህን ተከትሎ የተቋረጠው ጨዋታ ነገ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ከ30 አንስቶ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ከቆመበት ደቂቃ ጀምሮ እንደሚቀጥል ታውቋል። ጨዋታው እስከተቋረጠበት ደቂቃ ድረስም ሁለቱም ቡድኖች ግብ ሳያስቆጥሩ በባዶ ለባዶ ውጤት ላይ ነበሩ። በሌላ በኩል ዛሬ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ሊደረግ ታስቦ የነበረው እና በዝናብ ምክንያት ያልተካሄደው የወላይታ ድቻ እና የነገሌ አርሲ የ34ኛ ሳምንት ጨዋታ ሐሙስ ግንቦት 27 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ እንዲደረግ መወሰኑን ማህበሩ አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን መርሐ ግብር
May 29, 2026 298
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 34ኛ ሳምንት ዛሬ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ወላይታ ድቻ ከነገሌ አርሲ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ወላይታ ድቻ በ43 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው ነገሌ አርሲ በ52 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ወላይታ ድቻ የማሸነፍ መንገድን ለማግኘት ወደ ሜዳ ይገባል። ካለፉት ሁለት ጨዋታዎች አንድ ነጥብ ብቻ ያገኘው ነገሌ አርሲ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ እና በዋንጫ ፉክክሩ ለመቆየት ሶስት ነጥብ ማግኘት ይኖርበታል። ነገሌ አርሲ ካሸነፈ የሁለተኝነት ደረጃን ከመቻል የሚረከብ ሲሆን ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሶስት ዝቅ ያደርጋል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ከቀኑ ሰባት ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ42 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ46 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የ2016 ዓ.ም የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ33ኛ ሳምንት ከሀዲያ ሆሳዕና ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ አላገኘም። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። ፋሲል ከነማ ከሸገር ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በ33ኛ ሳምንት በኢትዮጵያ ቡና የ2 ለ 1 ሽንፈት ያስተናገደው ፋሲል ከነማ በ46 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሸገር ከተማ በ40 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ጨዋታው ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነታቸው ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ምድረ ገነት ሽሬ ከሀዲያ ሆሳዕና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረ ገነት ሽሬ በ37 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሀዲያ ሆሳዕና በ42 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ምድረ ገነት ሽሬ ከነገሌ አርሲ፣ ሀዲያ ሆሳዕና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር በተመሳሳይ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይፋለማሉ። በተለይም ምድረ ገነት ሽሬ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት ሶስት ነጥብ ማግኘት ግድ ይለዋል።
በወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኘው አርባምንጭ ከተማ ድል ቀንቶታል
May 28, 2026 694
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር አርባምንጭ ከተማ መቻልን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አሸናፊ ተገኝ እና ቴዎድሮስ በንቲ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ፈቱዲን ጀማል ለመቻል ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው አርባምንጭ ከተማ በ32 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት እያደረገ ባለው ትግል ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በሊጉም ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው መቻል በ53 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማጥበብ እድል አልተጠቀመበትም። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ34ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ሲዳማ ቡናን 2 ለ 1፣ ሀዋሳ ከተማ ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
ሀዋሳ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ድል ቀንቷቸዋል
May 28, 2026 579
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 20/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ መካሄድ ጀምሯል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። በረከት ሳሙኤል በ61ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት አስቆጥሯል። የሃዋሳ ከተማው የአማካይ ተጫዋች ያሬድ ብሩክ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ከ10 ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሃዋሳ ከተማ በ48 ነጥብ ደረጃውን ከሰባተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉም 12ኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ቡና በ46 ነጥብ ከነበረበት አምስተኛ ደረጃ ወደ ስድስተኛ ዝቅ ብሏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 1 ረቷል። ብሩክ አለማየሁ እና ሀብታሙ ጉልላት የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ጋር አገናኝተዋል። አስራት ቱንጆ የድሬዳዋ ከተማን ብቸኛ ግብ አስቆጥሯል። በሊጉ 12ኛ ድሉን ያስመዘገበው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ46 ነጥብ ከነበረበት 10ኛ ደረጃ ወደ 7ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ35 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት ስምንት የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ መቻል ከአርባምንጭ ከተማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም