ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
በአፍሪካ ዋንጫ ግብጽ ከቤኒን ናይጄሪያ ከሞዛምቢክ ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ ይጫወታሉ
Jan 5, 2026 52
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ የሶስተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ግብጽ ከቤኒን በአጋዲር ስታዲየም ከምሽት አንድ ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሰባት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋ ግብጽ በምድብ ሁለት በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ በመሆን 16 ውስጥ ገብታለች። ተጋጣሚዋ ቤኒን በምድብ አራት በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ በምርጥ ሶስተኝነት ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ዋንጫ አንድ ጊዜ ተገናኝተዋል። አንጎላ እ.አ.አ በ2010 ባዘጋጀችው 27ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሶስት ተገናኝተው ግብጽ በአህመድ ኤልሞሃመዲ እና ኢማድ ሞታይብ ግቦች ቤኒንን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ቡድኖቹ በሁሉም ውድድሮች አራት ጊዜ ተገናኝተው ግብጽ ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። ቤኒን እ.አ.አ በ2019 ግብጽ ባዘጋጀችው 32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ በመግባት በአህጉራዊ መድረክ የተሳትፎ ታሪኳ ምርጡን ውጤቷን አስመዝግባለች። የምዕራብ አፍሪካዋ ቤኒን ለሁለተኛ ጊዜ ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ ከሰባት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ግብጽ ጠንካራ ፈተና ይጠብቃታል። በሌላኛው የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ናይጄሪያ ከሞዛምቢክ ምሽት አራት ሰዓት ላይ በፌዝ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሶስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋ ናይጄሪያ በምድብ ሶስት በዘጠኝ ነጥብ በመሪነት ጨርሳለች። ሞዛምቢክ በምድብ ስድስት በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ መርጥ ሶስተኛ ሆና ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ሁለቱ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። አንጎላ እ.አ.አ በ2010 ባዘጋጀችው 27ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሶስት ተገናኝተው ናይጄሪያ ሞዛምቢክን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ፒተር ኦደምዊንጌ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኦባፌሚ ማርቲንስ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በአፍሪካ ዋንጫ ለአራተኛ ጊዜ እየተሳተፈች የሚገኘው ሞዛምቢክ በእስከ አሁን ተሳትፎዎቿ ከምድቧ አልፋ አታውቅም። የዛሬ ጨዋታዎች አሸናፊዎች በሩብ ፍጻሜው እርስ በእርስ ይገናኛሉ።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
Jan 5, 2026 48
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 27/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ ሳምንት በመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ መድን ከመቀሌ 70 እንደርታ ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በሊጉ ካደረጋቸው 12 ጨዋታዎች መካከል ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ12ቱ ጨዋታዎች ላይ 10 ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎች ተቆጥረውበታል። መድን በ13 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ በበኩሉ እስከ አሁን በሊጉ ያሸነፈው የጨዋታ ብዛት አንድ ብቻ ነው። አምስት ጊዜ ሲሸነፍ ስድስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 13 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 17 ጎሎችን አስተናግዷል። መቀሌ 70 እንደርታ በስምንት ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባህር ዳር ከተማ እስከ አሁን በሊጉ 12 ጨዋታዎችን ያደረገ ሲሆን በሶስቱ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። በስድስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። በ12ቱ ጨዋታዎች ላይ ዘጠኝ ጎሎችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ ዘጠኝ ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ15 ነጥብ 13ተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ ካደረጋቸው 12 ጨዋታዎች መካከል በአራቱ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። አራት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ጥሏል። ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ድሬዳዋ ከተማ በ16 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታሉ።
ካሜሮን ደቡብ አፍሪካን በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜ ገባች
Jan 5, 2026 85
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ተጠባቂ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ካሜሮን ደቡብ አፍሪካን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ማምሻውን በአል- መዲና ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ጁኒየር ቻማዱ በ34ኛው እና ክርስቲያን ኮፋኔ በ47ኛው ደቂቃ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኤቪደንስ ማክጎፓ በ88ኛው ደቂቃ ለደቡብ አፍሪካ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው አዝናኝ እና ተመጣጣኝ ፋክክር ለመመልከት ተችሏል። ድሉን ተከትሎ የአምስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ ባለቤት ካሜሮን ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅላለች። በሁለቱ ሀገራት የእርስ በእርስ ግንኙነት ታሪክ ካሜሮን በደቡብ አፍሪካ ላይ የመጀመሪያ ድሏን አስመዝግባለች። ካሜሮን በሩብ ፍጻሜው ከሞሮኮ ጋር የምታደርገው ጨዋታ ከወዲሁ ተጠባቂ ነው። አዘጋጇ ሞሮኮ ዛሬ ከታንዛንያ ጋር ባደረገችው የጥሎ ማለፍ ጨዋታ 1 ለ 0 በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜ ገብታለች።
በተጠባቂው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ እና ቼልሲ አቻ ተለያዩ
Jan 4, 2026 130
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ20ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ እና ቼልሲ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቲጃኒ ራይንደርስ በ42ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ማንችስተር ሲቲን መሪ አድርጓል። ኢንዞ ፈርናንዴዝ በ94ኛው ደቂቃ ላይ ከመረብ ባሳረፈው ግብ ቼልሲ አቻ ወጥቷል። ባለሜዳው ማንችስተር ሲቲ በኳስ ቁጥጥር እና ኢላማ የጠበቁ ሙከራዎችን በማድረግ የተሻለ ነበር። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ ስድስት ከፍ ብሏል። ቼልሲ በ31 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ሊድስ ዩናይትድ አንድ አቻ ሲለያይ፣ የፉልሃም እና ሊቨርፑል ጨዋታ ሁለት አቻ ተጠናቋል። ብሬንትፎርድ ኤቨርተንን 4 ለ 2፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ክሪስታል ፓላስን 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ሰንደርላንድ አንድ አቻ ተለያይተዋል። የዛሬ ጨዋታዎችን ተከትሎ የ20ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ21ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከታህሳስ 28 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳሉ።
ሲዳማ ቡና ሀድያ ሆሳዕናን በማሸነፍ የሊጉን መሪነት አጠናከረ
Jan 4, 2026 90
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና ሀድያ ሆሳዕናን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ መስፍን ታፈሰ እና ዮሴፍ ዮሐንስ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ከሶስት ተከታታይ ድሎች በኋላ ሽንፈት ያስተናገደው ሀድያ ሆሳዕና በ16 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በሌሎች ጨዋታዎች ምድረገነት ሽሬ ኢትዮጵያ ቡናን 3 ለ 1 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሽመክት ጉግሳ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ዳንኤል ዳርጌ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። አቡበከር አዳሙ በፍጹም ቅጣት ምት ለኢትዮጵያ ቡና ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ ሸገር ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ዳዊት ካሳው በጨዋታ ለሸገር ከተማ በጨዋታ፣ አዲስ ግደይ በፍጹም ቅጣት ምት ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በዕለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ ነጌሌ አርሲ መቻልን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳዊት ተፈሪ እና አለኝታ ማርቆስ ግቦቹን አስቆጥረዋል።
አዘጋጇ ሞሮኮ ለሩብ ፍጻሜ አለፈች
Jan 4, 2026 82
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ሞሮኮ ታንዛንያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብራሂም ዲያዝ በ64ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል ሀገሩን አሸናፊ አድርጓል። ዲያዝ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ አራት ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን መምራት ጀምሯል። የሞሮኮው ኢስማኤል ሳይባሪ በ15ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ከጨዋታ ውጪ በመሆኑ ተሽሯል። በጨዋታው ላይ ሞሮኮ ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ውጤቱን ተከትሎ አዘጋጇ ሞሮኮ ሩብ ፍጻሜ የተቀላቀለች ሶስተኛ ሀገር ሆናለች። ሞሮኮ በሩብ ፍጻሜው ከደቡብ አፍሪካ እና ካሜሮን አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ደቡብ አፍሪካ ከካሜሮን በአል -መዲና ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
በፕሪሚየር ሊጉ ሽረ ምድረ ገነት ኢትዮጵያ ቡናን አሸንፏል
Jan 4, 2026 80
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 26/2018 (ኢዜአ)፡- በ2018 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሣምንት ጨዋታ ሽረ ምድረ ገነት ኢትዮጵያ ቡናን 3 ለ 1 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲም በተካሄደው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ፤ ዳንኤል ዳርጌ እና ሽመክት ጉግሳ (2) ባስቆጠሯቸው ግቦች ሽረ ምድረ ገነት ተጋጣሚውን ረትቷል። በአንጻሩ የኢትዮጵያ ቡናን ብቸኛ ግብ አቡበከር አዳሙ በፍጹም ቅጣት ምት አስቆጥሯል። እንዲሁም በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደረጉት ሸገር ከተማ እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ግቦቹንም ዳዊት ካሳው በጨዋታ ለሸገር ከተማ እንዲሁም አዲስ ግደይ በፍጹም ቅጣት ምት ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመረብ አሳርፈዋል። ቀደም ብሎ 7 ሠዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው የ13ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ጨዋታ በዳዊት ተፈራ እና አለኝታ ማርቆስ ግቦች ነጌሌ አርሲ መቻልን 2 ለ 0 አሸንፏል።
ሊድስ ዩናይትድ እና ማንቼስተር ዩናይትድ ነጥብ ተጋሩ
Jan 4, 2026 63
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 26/2018(ኢዜአ)፡- በ20ኛ ሣምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሊድስ ዩናይትድ ማንቼስተር ዩናይትድን በሜዳው አስተናግዶ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተለያይተዋል። የሊድስ ዩናይትድን ግብ በ62ኛው ደቂቃ አሮንሰን ከመረብ አሳርፏል። የማንቼስተር ዩናይትድን ግብ ደግሞ ኩና በ65ኛው ደቀቂቃ ማስቆጠር ችሏል። ውጤቱን ተከትሎ ማንቼስተር ዩናይትድ በ31 ነጥብ አንድ ደረጃ ከፍ ብሎ 5ኛ ላይ ተቀምጧል። እንዲሁም ሊድስ ዩናይትድ በነበረበት 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ነጌሌ አርሲ መቻልን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሶስተኛ ከፍ አደረገ
Jan 4, 2026 58
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ነጌሌ አርሲ መቻልን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳዊት ተፈራ በ11ኛው እና አለኝታ ማርቆስ በ31ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ነጌሌ አርሲ በ22 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው መቻል በ20 ነጥብ ከነበረበት ስድስተኛ ደረጃ ወደ ሰባተኛ ዝቅ ብሏል።
የአፍሪካ ዋንጫን ለበርካታ ጊዜ ያዘጋጁ ሀገራት
Jan 4, 2026 94
የአፍሪካ ዋንጫ ከተጀመረ 68 ዓመታትን አስቆጥሯል። እ.አ.አ በ1957 የተካሄደውን የመጀመሪያውን የአፍሪካ ዋንጫ ያዘጋጀችው የምስራቅ አፍሪካዊቷ ሀገር ሱዳን ናት። በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ 19 ሀገራት ውድድሩን ለብቻ ወይም በጣምራ አዘጋጅተዋል። ግብጽ የአፍሪካ ዋንጫን አምስት ጊዜ በማስተናገድ ቀዳሚውን ስፍራ ይዛለች። ካዘጋጀቻቸው ውድድሮች መካከል ሶስቱን በሀገሯ አስቀርታለች። የምዕራብ አፍሪካዊቷ ሀገር ጋና አራት ጊዜ ውድድሩን በማዘጋጀት ሁለተኛ ደረጃ ላይ ስትቀመጥ ከዚህ ውስጥ በአንድ አጋጣሚ ዋንጫውን አንስታለች። ኢትዮጵያ እና ቱኒዚያ በተመሳሳይ ሶስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አዘጋጅተዋል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1962 ባዘጋጀችው ሶስተኛ የአፍሪካ ዋንጫ ግብጽን በፍጻሜው 4 ለ 2 በመርታት ብቸኛ ዋንጫውን አንስታለች። እ.አ.አ በ1968 ባዘጋጀችው ስድስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ዋንጫውን አንስታለች። ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን ያዘጋጀችው እ.አ.አ በ1976 10ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ሲሆን በፍጻሜው ሞሮኮ ጊኒን በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ሞሮኮ፣ ካሜሮን፣ ሱዳን፣ ኮትዲቯር፣ ጋቦን፣ ደቡብ አፍሪካ እና ኢኳቶሪያል ጊኒ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አዘጋጅተዋል። የዘንድሮውን ጨምሮ ከ35ቱ የአፍሪካ ዋንጫዎች መካከል ሁለቱ ብቻ ናቸው በጣምራ የተዘጋጁት። ሞሮኮ እ.አ.አ 1988 ካዘጋጀችው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በኋላ ውድድሩን በድጋሚ የማስተናገድ እድል ተሰጥቷታል። እ.አ.አ በ2027 የሚካሄደውን 36ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ዩጋንዳ፣ ኬንያ እና ታንዛንያ በጣምራ ያዘጋጃሉ። ይህም ሀገራቱ ውድድሩን ለመጀመሪያ ጊዜ በጋራ የማዘጋጀት እድል ሰጥቷቸዋል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2029 የሚካሄደውን 37ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት ጥያቄ ማቅረቧ ይታወቃል።
ማንችስተር ሲቲ ከቼልሲ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 4, 2026 100
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ስድስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ማንችስተር ሲቲ ከቼልሲ በኢትሃድ ስታዲየም ይጫወታሉ። ማንችስተር ሲቲ በ41 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቼልሲ በ30 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ57ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 56 ጨዋታዎች ቼልሲ 27 ጊዜ ሲያሸንፍ፣ ማንችስተር ሲቲ 20 ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ ዘጠኝ ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች በነበራቸው የእርስ በእርስ ግንኙነት ማንችስተር ሲቲ ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ነጥብ ተጋርተዋል። ማንችስተር ሲቲ በ19ኛ ሳምንት ከሰንደርላንድ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ከአሰልጣኝ ኢንዞ ማሬስካ ጋር የተለያየው ቼልሲ በበኩሉ ባለፉት ሶስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ማንችስተር ሲቲ ካሸነፈ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት መልሶ ወደ አራት ዝቅ ያደርጋል። ቼልሲ ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። የ40 ዓመቱ ማይክል ኦሊቨር ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ሊድስ ዩናይትድ ከማንችስተር ዩናይትድ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 እና ፉልሃም ከሊቨርፑል ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከሰንደርላንድ፣ ኤቨርተን ከብሬንትፎርድ እና ኒውካስትል ዩናይትድ ከክሪስታል ፓላስ በተመሳሳይ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከሀድያ ሆሳዕና ይጫወታል
Jan 4, 2026 69
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ሀድያ ሆሳዕና ከሲዳማ ቡና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሀድያ ሆሳዕና በሊጉ 12 ጨዋታዎችን አከናውኖ አራት ጊዜ ድል ሲቀናው በተመሳሳይ አራት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ቡድኑ በ16 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በበኩሉ በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 12 ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ሲያሸንፍ ሽንፈት ያስተናገደው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። አራት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። ሲዳማ ቡና በ25 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ሲዳማ ካሸነፈ መሪነቱን ያጠናክራል። ሀድያ ሆሳዕና ድል ከቀናው አራተኛ ተከታታይ የሊግ ድሉን ያስመዘግባል። ነጌሌ አርሲ ከመቻል ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ነጌሌ አርሲ በውድድር ዓመቱ 12 ጨዋታዎችን አድርጎ አምስቱን ሲያሸንፍ በሶስቱ ተሸንፏል። በአራቱ ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ 19 ነጥብ በመሰብሰብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው መቻል በሊጉ ካከናወናቸው 12 ጨዋታዎች መካከል በአራቱ ድል ሲቀዳጅ ሁለት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪዎቹ ስድስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። ቡድኑ በ20 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው ነጌሌ አርሲ በድል ጉዞ ለመቀጠል፣ መቻል ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። ሸገር ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በ12 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ15 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሸገር ከተማ ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል ለመመለስ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ቡና ከምድረ ገነት ሽሬ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ቡና በ15 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ምድረ ገነት ሽሬ በ14 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ጨዋታው ኢትዮጵያ ቡና ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ፣ ምድረ ገነት ሽሬ ከአራት ተከታታይ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
በጥሎ ማለፉ አዘጋጇ ሞሮኮ ከታንዛንያ ደቡብ አፍሪካ ከካሜሮን የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Jan 4, 2026 84
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። አዘጋጇ ሞሮኮ ከታንዛንያ ምሽት አንድ ሰዓት በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሞሮኮ በምድብ አንድ ሰባት ነጥብ በመሰብሰብ አንደኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። የምስራቅ አፍሪካዋ ታንዛንያ በምድብ ሶስት በሁለት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ ምርጥ ሶስተኛ ሆና ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ሁለቱ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። ኮትዲቯር እ.አ.አ በ2023 ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አራት ተገናኝተው ሞሮኮ ታንዛንያን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ሮማን ሳይስ፣ አዝዲን ኡናሂ እና የሱፍ ኤን-ኔይስሪ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሶስቱም ተጫዎቾች በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ የሞሮኮ ስብስብ ውስጥ ይገኛሉ። ታንዛንያ ወደ ሩብ ለፍጻሜ ለመግባት በአፍሪካ ምርጡ ብሄራዊ ቡድን የሚል ስያሜ ያገኘውን ሞሮኮን የማሸነፍ ጠንካራ ፈተና ይጠብቃታል። በሌላኛው መርሃ ግብር ምሽት አራት ሰዓት ላይ ደቡብ አፍሪካ ከካሜሮን በአል መዲና ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ደቡብ አፍሪካ በምድብ ሁለት በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በምድብ ስድስት የነበረችው ካሜሮን በሰባት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቅ 16ቱን ተቀላቅላች። ሀገራቱ በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ1996 ባዘጋጀችው 20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው አዘጋጇ ሀገር 3 ለ 0 አሸንፋለች። ፊሊሞን ማሲንጋ፣ ማርክ ዊሊያምስ እና ጆን ሌሲባ ሞሾዩ ግቦችን አስቆጥረዋል። በሁሉም ውድድሮች ባደረጓቸው ስምንት ጨዋታዎች ደቡብ አፍሪካ አምስት ጊዜ ስታሸንፍ አምስት ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። ደቡብ አፍሪካ አንድ ጊዜ፣ ካሜሮን አምስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አሸንፈዋል። በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ በምድባቸው ጥሩ ብቃት ያሳዩት ሀገራት የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የዛሬ ጨዋታ አሸናፊዎች በሩብ ፍጻሜው የሚጫወቱ ይሆናል። ትናንት በተደረጉ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ሴኔጋል እና ማሊ ለሩብ ፍጻሜ አልፈዋል።
አርሰናል ቦርንማውዝን በማሸነፍ የሊጉን መሪነት አጠናከረ
Jan 3, 2026 108
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርሰናል ቦርንማውዝን 3 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በቫይታሊቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ዴክላን ራይስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ጋብርኤል ማጋሌሽ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ኢቫኒልሰን እና ጁኒየር ክሩፒ ለቦርንማውዝ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ለኢቫኒልሰን ጎል መቆጠር ትልቅ ስህተት ሰርቶ የነበረው የአርሰናሉ ተከላካይ ጋብርኤል ማጋሌሽ ለመድፈኞቹ ግብ በማስቆጠር ቡድኑን ክሷል። አርሰናል በሁለተኛው አጋማሽ የወሰደው ብልጫ ጨዋታውን እንዲያሸንፍ አስችሎታል። በውድድር ዓመቱ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው የሊጉ መሪ አርሰናል ነጥቡን ወደ 48 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ አስቶንቪላ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ስድስት ከፍ ማድረግ ችሏል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቦርንማውዝ በ23 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቡድኑ የዛሬውን ጨምሮ ባለፉት 11 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።
ሴኔጋል ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀለች የመጀመሪዋ ሀገር ሆነች
Jan 3, 2026 87
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ጥሎ ማለፍ ጨዋታ ሴኔጋል ሱዳንን 3 ለ 1 አሸንፋለች። ማምሻውን በታንጀር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አሚር አብደላህ በስድስተኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ ሱዳን ሳትጠበቅ መሪ መሆን ችላ ነበር። ይሁንና ፓፓ ጌይ በ29ኛው ደቂቃ እና በመጀመሪያው አጋማሽ የባከነ ሰዓት ጭማሪ እንዲሁም ተቀይሮ የገባው ታዳጊው ኢብራሂም እምባይ በ77ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ላይ ሴኔጋል በሱዳን ላይ ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ድሉን ተከትሎ ሴኔጋል ሩብ ፍጻሜ የገባች የመጀመሪያ ሀገር ሆናለች። በሩብ ፍጻሜው ከማሊ እና ታንዛንያ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ማሊ እና ቱኒዚያ ምሽት አራት ሰዓት ላይ በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
አርባምንጭ ከተማ እና ሃዋሳ ከተማ አቻ ተለያዩ
Jan 3, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርባምንጭ ከተማ እና ሃዋሳ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተከናውኗል። ውጤቱን ተከትሎ አርባምንጭ ከተማ በሰባት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው። ሃዋሳ ከተማ በ21 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረጉ የ13ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ወላይታ ድቻ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። አዳማ ከተማ ከፋሲል ከነማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በተመሳሳይ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ነጥብ ተጋርተዋል
Jan 3, 2026 76
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ኢትዮ ኤሌትሪክ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በአዲስ አበባ ስታዲየም ተካሂዷል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ21 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ10 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል።
አስቶንቪላ ኖቲንግሃም ፎረስትን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Jan 3, 2026 73
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ20ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ አስቶንቪላ ኖቲንግሃም ፎረስትን 3 ለ 1 አሸንፏል። በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆን ማክጊን ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኦሊ ዋትኪንስ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ 13ኛ ድሉን ያስመዘገበው አስቶንቪላ በ42 ነጥብ ከሶስተኛ ደረጃ ወደ ሁለተኛ ከፍ ብሏል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኖቲንግሃም ፎረስት በ18 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። ሞርጋን ጊብስ-ዋይት ለኖቲንግሃም ፎረስት ብቸኛውን ግብ አስቆጥሯል።
ወላይታ ድቻ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ አቻ ተለያዩ
Jan 3, 2026 63
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት ወላይታ ድቻ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቴዎድሮስ ኃይለማርያም በ40ኛ ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ወላይታ ድቻ መሪ መሆን ችሎ ነበር። ይሁንና ከእረፍት መልስ አቤል ያለው በ67ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ግብ ለቅዱስ ጊዮርጊስ አንድ ነጥብ አስገኝታለች። ወላይታ ድቻ በ12 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ቅዱስ ጊዮርጊስ በ19 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ክለቡ ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም።
አዳማ ከተማ እና ፋሲል ከነማ ነጥብ ተጋሩ
Jan 3, 2026 69
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ አዳማ ከተማ እና ፋሲል ከነማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በአዲስ አበባ ስታዲየም ተካሂዷል። አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። ፋሲል ከነማ በ25 ነጥብ ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር በነጥብ እኩል ቢሆንም በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ፋሲል ከነማ በሊጉ ሽንፈት ያላስተናገደ ብቸኛው ቡድን ነው።