ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ባህር ዳር ከተማ የውድድር ዓመቱን በድል ቋጭቷል
May 15, 2026 51
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ባህር ዳር ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አስቴር ደግአረገ እና ወርቅነሽ መሰለ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ረድኤት ዳንኤል ለልደታ ክፍለ ከተማ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፋለች። የባህር ዳር ከተማዋ ወርቅነሽ መሰለ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ ሰባተኛ ድሉን ያስመዘገበው ባህር ዳር ከተማ ደረጃውን ከ11ኛ ወደ 10ኛ ከፍ አድርጓል። ዓመቱንም በድል አጠናቋል። በውድድር ዓመቱ 16ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ልደታ ክፍለ ከተማ በተመሳሳይ 22 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍፃሜ መርሐ ግብር የሚደረግባቸው ቀናቶች ይፋ ሆኑ
May 15, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍፃሜ ድልድል ትናንት መውጣቱ ይታወቃል። በእጣው መሰረት ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ መድን፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ 70 እንደርታ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጨዋታዎቹ የሚደረግባቸውን ቀናት እና የመጫወቻ ሜዳ ዛሬ ይፋ አድርጓል። በዚሁ መሰረት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ 70 እንደርታ ግንቦት 17፣ ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ መድን ግንቦት 18 በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ።
በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉባቸው ውድድሮች
May 15, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ አራተኛ ቀኑን ይዟል። ምሽት 2 ሰዓት ከ05 ላይ የ10000 ሜትር ሴቶች የፍጻሜ ውድድር ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ አሰፉ አብርሃ፣ ስምረት በርሄ እና ዘይን አየልኝ ኢትዮጵያን ወክለው ይሳተፋሉ። አትሌት ዘይን አየልኝ በ5000 ሴቶች የነሐስ ሜዳሊያ ማግኘቷ ይታወሳል። አትሌት ጌታሁን ታደሰ ምሽት 1 ሰዓት ከ45 ላይ በሚካሄደው የወንዶች የ110 ሜትር መሰናክል የማጣሪያ ውድድር ላይ ይሳተፋል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው ሶስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና ሶስት የነሐስ በድምሩ ሰባት ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። የአትሌቲክስ ሻምፒዮናው ከነገ በስቲያ ይጠናቀቃል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች
May 15, 2026 127
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። የዕለቱ ቀዳሚ መርሐ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድንን ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ያገናኛል። መቀሌ 70 እንደርታ በ30 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ኢትዮጵያ መድን በ40 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች አሸንፏል። ጨዋታው መቀሌ 70 እንደርታ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ኢትዮጵያ መድን በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው። ድሬዳዋ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ያላገኘው ድሬዳዋ ከተማ በ34 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሉ። ባህር ዳር ከተማ በ41 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ባህር ዳር ከተማ በዘንድሮው የውድድር ዓመት በርካታ የአቻ ውጤቶችን (17 ጊዜ) ያስመዘገበ ቡድን ነው። ሁለቱም ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ38 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሸገር ከተማ በ40 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኢትዮጵያ መድን የ2 ለ 1 ሽንፈት ሲያስተናግድ ሸገር ከተማ የሊጉን መሪ ሲዳማ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታው ንግድ ባንክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ሸገር ከተማ በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የማጠናቀቂያ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ
May 15, 2026 109
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይደረጋሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ልደታ ክፍለ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ይጫወታሉ። ልደታ ክፍለ ከተማ በ22 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በ19 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በ26ኛ ሳምንት ወራጁን አርባምንጭ ከተማን 4 ለ 1 ያሸነፈው ልደታ ክፍለ ከተማ ዓመቱን በድል ለመቋጨት ይጫወታል። በ26ኛ ሳምንት በአዲስ አበባ ከተማ 3 ለ 1 የተሸነፈው ባህር ዳር ከተማ ዓመቱን ድል ለማሳረግ ወደ ሜዳ ይገባል። በሌላኛው መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና በ35 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ መውረዱ የተረጋገጠው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። በ25ኛ ሳምንት ይርጋጨፌ ቡና ያለ ግብ አቻ የተለያየው ሲዳማ ቡና ዓመቱን በማሸነፍ ለመፈጸም ይጫወታል። ከፕሪሚየር ሊጉ ለወረደው አርባምንጭ ከተማ ጨዋታው ከመርሐ ግብር ማሟያነት የዘለለ ትርጉም የለውም። ሃዋሳ ከተማ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሃዋሳ ከተማ በ49 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ43 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች ዓመቱን በድል ለማጠናቀቅ የሚያደርጉት ፍልሚያ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ66 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በተመሳሳይ 66 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰሎሞን በ24 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራች ይገኛል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ ደግሞ በ20 ግቦች ተከታዩን ስፍራ ይዛለች።
አስቶንቪላ ከሊቨርፑል- የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎን ለማግኘት የሚደረግ ፍልሚያ
May 15, 2026 105
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። ምሽት አራት ሰዓት ላይ አስቶንቪላ ከሊቨርፑል በቪላ ፓርክ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሊቨርፑል እና አስቶንቪላ በተመሳሳይ 59 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው በቅደም ተከተል አራተኛ እና አምስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ባለሜዳው አስቶንቪላ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑልም ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። የዛሬው ጨዋታ አሸናፊ የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን ያረጋግጣል። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ40 ዓመቱ ክሪስ ካቫናግ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት እስከ ግንቦት 11 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዝግጅት
May 14, 2026 224
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከብሩንዲ ጋር ለሚያደርገው ሁለተኛ ዙር የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታ የሁለተኛ ቀን ልምምዱን ዛሬ አድርጓል። አሰልጣኝ ራውዳ ዓሊ ለ30 ተጫዋቾች ጥሪ በማድረግ ትናንት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሜዳ ዝግጅታቸውን የጀመሩ ሲሆን ጥሪ የተደረገላቸው ተጫዋቾች ሁሉም ተገኝተው ልምምዳቸውን አከናውነዋል። በብሔራዊ ቡድኑ የሁለተኛ ቀን ዝግጅት ተጫዋቾች የእርስ በእርስ ጨዋታዎችን በማድረግ አቋማቸውን መፈተሻቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከብሩንዲ ጋር ግንቦት 16 የመጀመሪያ ጨዋታውን በሜዳው፣ የመልስ ጨዋታውን ግንቦት 23 ቡጁምቡራ ላይ ያከናውናል። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። በማጣሪያ የሚያልፉ አራት የአፍሪካ ሀገራት በሶስት ዙሮች በሚደረጉ ጨዋታዎች ይለያሉ።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሶስተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 14, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ ሶስተኛ ቀኑን ባስቆጠረው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተለያዩ ውድድሮች በመካሄድ ላይ ናቸው። ማምሻውን በተደረገው የ3000 ሜትር መሰናክል የወንዶች የፍጻሜ ውድድር አትሌት ገመቹ ጎዳና 8 ደቂቃ ከ41 ሴኮንድ ከ02 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ ወጥቷል። አትሌት ገመቹ ለኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ሶስተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አስገኝቷል። በውድድሩ ላይ የተሳተፈው ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ሳሙኤል ፍሬው ሶስተኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳሊያ ባለቤት ሆኗል። በ800 ሜትር ሴቶች ፍፃሜ አትሌት ምስጋና ኃይሉ እና በ400 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ አትሌት አጃይባ አልዩ የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘታቸው ይታወቃል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው ሶስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና ሶስት የነሐስ በድምሩ ሰባት ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
አንጋፋው የእግር ኳስ ሰው ጌታቸው ገብረማርያም ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ
May 14, 2026 156
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጫዋች፣ ዓለም አቀፍ ዳኛ እና አመራር የነበሩት ጌታቸው ገብረማርያም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ጌታቸው ገብረማርያም በተጫዋችነት ለኦሜድላ እና ጥጥ ማኅበር እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጫውተው ያሳለፉ ሲሆን በመቀጠል ለረጅም ዘመናት በዓለም አቀፍ ዳኝነት ጭምር በሚታወቁበት የዳኝነት ሙያ አገልግለዋል። ከዳኝነት ከተገለሉ በኋላም በኮሚሽነርነት፣ በአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንትነት እንዲሁም በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች በጥቅሉ ከ60 ዓመታት በላይ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ላይ በማገልገል ማሳለፋቸውን ፌዴሬሽኑ ገልጿል። የአቶ ጌታቸው ገብረማርያም ሥርዓተ ቀብር ነገ በአማኑኤል ቤተ-ክርስቲያን ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ይፈፀማል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በአንጋፋው የእግር ኳስ ሰው ጌታቸው ገብረማርያም ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን በመግለጽ ለቤተሰብ፣ ለወዳጅ ዘመድ፣ ለእግር ኳስ ቤተሰብ እና ለሙያ ባልደረቦች መፅናናትን ተመኝቷል።
በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 14, 2026 131
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በ24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። በ800 ሜትር ሴቶች ፍፃሜ አትሌት ምስጋና ኃይሉ 1 ደቂቃ ከ59 ሴኮንድ ከ02 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት አንደኛ ወጥታለች። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ሁለተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። ትዕግስት አያና ስድስተኛ እና ሀብታም ገበየሁ ሰባተኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል። በ400 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ አትሌት አጃይባ አልዩ የመጀመሪያውን ወርቅ ለኢትዮጵያ ማስገኘቷ ይታወቃል። በ800 ሜትር ፍጻሜ ቦትስዋናዊቷ ኖዌ ኦራቲሌ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ስትጨርስ የኒጀሯ አትሌት ቡባከር ሰሚራ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቃለች። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው ሁለት የወርቅ፣ አንድ የብር እና አንድ የነሐስ በድምሩ አራት ሜዳሊያዎችን አግኝታለች።
በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 14, 2026 86
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ሶስተኛ ቀኑን ይዟል። በ400 ሜትር የሴቶች ፍፃሜ ውድድር አትሌት አጃይባ አልዩ 51 ሴኮንድ ከ54 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት አንደኛ በመውጣት አሸንፋለች። ይህም ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ያገኘችው የመጀመሪያው የወርቅ ሜዳሊያ ሆኖ ተመዝግቧል። ኢትዮጵያ እምብዛም በማትታወቅበት የአጭር ርቀት ሩጫ ወርቅ ማግኘቷ ተስፋን የፈነጠቀ ሆኖ ተገኝቷል። ቦትስዋናዊቷ ካምቤሩካ ኦባኬንግ ሁለተኛ እና ጋናዊቷ አጄማንግ ፍሎረንስ ሶስተኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው አንድ የወርቅ፣ አንድ የብር እና አንድ የነሐስ በድምሩ ሶስት ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
መቻል ወደ ሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና የተጠጋበትን ወሳኝ ድል አስመዘገበ
May 14, 2026 88
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር መቻል ነገሌ አርሲን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቸርነት ጉግሳ፣ በረከት ደስታ፣ ዩጋንዳዊው ቻርልስ ሙሲጌ እና ፈቱዲን ጀማል (በፍጹም ቅጣት ምት) ግቦቹን አስቆጥረዋል። ከተከታታይ የአቻ ውጤቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው መቻል በ52 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። መቻል ከመሪው ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት በማጥበብ የዋንጫ ተፎካካሪነቱን አጠናክሯል። በውድድር ዓመቱም 13ኛ ድሉን አስመዝግቧል። ከተከታታይ ድሎች በኋላ ሽንፈት ያስተናገደው ነገሌ አርሲ በ51 ነጥብ ከሁለተኛ ደረጃ ወደ ሶስተኛ ዝቅ ብሏል። በሊጉም ሰባተኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በዋንጫ ፉክክሩም ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥሏል። ዛሬ በተደረጉ የ32ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ሀዲያ ሆሳዕና የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡናን፣ ምድረ ገነት ሽሬ ኢትዮጵያ ቡናን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ወላይታ ድቻ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ወላይታ ድቻ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ነጥብ ተጋሩ
May 14, 2026 94
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ወላይታ ድቻ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። የቡድኖቹ ጨዋታ በአዲስ አበባ ስታዲየም ተካሄዷል። ከተከታታይ ድሎች በኋላ ነጥብ የጣለው ወላይታ ድቻ በ42 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ቅዱስ ጊዮርጊስ በበኩሉ፣ የነጥብ መጠኑን 40 በማድረስ በሰንጠረዡ 13ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
በወራጅ ቀጠና የሚገኘው ምድረ ገነት ሽሬ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
May 14, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ምድረ ገነት ሽሬ ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አቤል እንዳለ በ12ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ድሉን ያስመዘገበው ምድረ ገነት ሽሬ በ36 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ላለመውረድ እያደረገ ባለው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ሆኖም ግን፣ በተመሳሳይ 36 ነጥብ ካለው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር እኩል ቢሆንም፣ በግብ ልዩነት ተበልጦ 17ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ቡና በ43 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡናማዎቹ ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ድል አልቀናቸውም።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ተከታታይ ሽንፈቱን አስተናገደ
May 14, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ሀዲያ ሆሳዕና ሲዳማ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ደስታ ዋሚሾ በ62ኛው ደቂቃ ግቡን አስቆጥሯል። በሊጉ ተከታታይ ሽንፈቱን ያስተናገደው የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና 55 ነጥብ ላይ ረግቷል። ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ድል ያልቀናው ሲዳማ ቡና በጥሩ ወቅታዊ ብቃት ላይ አይገኝም። በውድድር ዓመቱ የተሸነፈባቸው ጨዋታዎች ብዛትም ሰባት ደርሰዋል። ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው ሀዲያ ሆሳዕና በ41 ነጥብ ከነበረበት 15ኛ ደረጃ ወደ 10ኛ ከፍ ብሏል። በሊጉም 10ኛ ድሉን አስመዝግቧል።
ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ መድን ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ 70 እንደርታ በኢትዮጵያ ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ ይገናኛሉ
May 14, 2026 127
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ ድልድል ዛሬ የክለብ ተወካዮች እና የውድድር አመራሮች በተገኙበት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጽሕፈት ቤት ወጥቷል። በእጣው መሰረት ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ መድን ፣ ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከ መቀሌ 70 እንደርታ የሚጫወቱ ይሆናል። የጨዋታ ቀናት ወደፊት እንደሚገለጽ ፌዴሬሽኑ አስታውቋል።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከሀዲያ ሆሳዕና መቻል ከነገሌ አርሲ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
May 14, 2026 132
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ዛሬ በሚደረጉ አራት ጨዋታዎች ይጀመራል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ሲዳማ ቡና ከሀዲያ ሆሳዕና በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሲዳማ ቡና በ55 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዟል። ሀዲያ ሆሳዕና በ38 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሲዳማ ቡና ወደ አሸናፊነት ለመመለስ እና መሪነቱን ለማጠናከር ይፋለማል። በ31ኛ ሳምንት ሃዋሳ ከተማን 1 ለ 0 የረታው ሀዲያ ሆሳዕና ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ መቻል ከነገሌ አርሲ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታም ትኩረት ስቧል። መቻል በ49 ነጥብ ሶስተኛ፣ ነገሌ አርሲ በ51 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው መቻል ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። ተጋጣሚው ነገሌ አርሲ ተከታታይ የሊግ ድሎችን ያስመዘገበ ሲሆን ሶስት ነጥብ በዋንጫ ፉክክሩ እንዲቆይ ያደርገዋል። በሊጉ አናት ላይ የሚገኙ ክለቦች የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች በዋንጫ ፉክክሩ ላይ ተጽእኖ የሚያሳድሩ ናቸው። ወላይታ ድቻ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ያሸነፈው ወላይታ ድቻ በ41 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ39 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ በ31ኛ ሳምንት መቀሌ 70 እንደርታን 1 ለ 0 አሸንፏል። ሁለቱ ቡድኖች በድል ጉዟቸው ለመቀጠል የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ምድረ ገነት ሽሬ ከኢትዮጵያ ቡና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ምድረ ገነት ሽሬ በ33 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኢትዮጵያ ቡና በ43 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት በአዳማ ከተማ የ4 ለ 0 ሽንፈት ያስተናገደው ምድረገነት ሽሬ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሁለቱም የአሸናፊነት መንገድን ለማግኘት ይጫወታሉ። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት እስከ ግንቦት 8 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። አቤል ያለው ከሲዳማ ቡና የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በ14 ጎሎች እየመራ ነው። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጫዋቾች የሆኑት አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል በተመሳሳይ 10 ግቦች ይከተላሉ።
ኢንተር ሚላን በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ዋንጫውን አነሳ
May 14, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በጣልያን የጥሎ ማለፍ ዋንጫ (ኮፓ ኢጣሊያ) የፍጻሜ ጨዋታ ኢንተር ሚላን ላዚዮን 2 ለ 0 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በስታዲዮ ኦሎምፒኮ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ላውታሮ ማርቲኔዝ እና የላዚዮው ተከላካይ አዳም ማሩሲች በራሱ ላይ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ኢንተር ሚላን ለ10ኛ ጊዜ የጥሎ ማለፉን ዋንጫ አንስቷል። በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ዋንጫውን አስገብቷል። ኢንተር ባለፈው ሳምንት የሴሪአውን ዋንጫ ለ21ኛ ጊዜ ማንሳቱ የሚታወስ ነው። የዛሬው የፍጻሜ ተፋላሚ ላዚዮ የጥሎ ማለፉን ዋንጫን ከሰባት ዓመታት በኋላ የማንሳት ህልሙ አልተሳካም። የሮሙ ክለብ የኮፓ ኢጣሊያን ሰባት ጊዜ አሸንፏል።
ፒኤስጂ የፈረንሳይ ሊግ ዋን አሸናፊ መሆኑን አረጋገጠ
May 14, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በፈረንሳይ ሊግ ዋን የ29ኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሐ ግብር ፒኤስጂ ሌንስን 2 ለ 0 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በቦላሬት- ዴሌሊስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ክቪቻ ክቫራትስኬሊያ እና ኢብራሂም ምባዬ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። በውድድር ዓመቱ ለ24ኛ ጊዜ ድል የቀናው ፒኤስጂ በ76 ነጥብ አንድ ጨዋታ እየቀረው የሊጉ አሸናፊ መሆኑን አረጋግጧል። የሊጉን ዋንጫ ሲያነሳ የአሁኑ ለ14ኛ ጊዜ ነው። ፒኤስጂ ካለፉት 13 የሊግ ዋንጫዎች 11ዱን በማንሳት ፍጹም የበላይነቱን ይዟል። በሊጉ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሌንስ በ67 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ሌንስ ዋንጫውን ለማንሳት ያደረገው ብርቱ ፉክክር አድናቆት አስችሮታል።
ማንችስተር ሲቲ ወሳኝ ድል ተቀዳጀ
May 14, 2026 134
አዲስ አበባ፤ ግንቦት6/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ31ኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሐ ግብር ማንችስተር ሲቲ ክሪስታል ፓላስን 3 ለ 0 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶዋን ሴሜንዮ ፣ ኦማር ማርሙሽ እና ሳቪኒዮ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ባለሜዳው ሲቲ ሙሉ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። በሊጉ 23ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ በ77 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ አድርጓል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በሊጉ መሪ አርሰናል ላይ ጫና ማሳደሩን ቀጥሏል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 14ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ክሪስታል ፓላስ በ44 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።