ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ኤቨርተን ቼልሲን አሸነፈ
Mar 21, 2026 127
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 31ኛ ሳምንት ኤቨርተን ቼልሲን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሂል ዲኪንሰን ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቤቶ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኢሊማን ንዳዬ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ቼልሲ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ኤቨርተን ኢላማቸውን የጠበቁ ሙከራዎችን በማድረግ ተሽሎ ተገኝቷል። ውጤቱን ተከትሎ በሊጉ 13ኛ ድሉን ያስመዘገበው ኤቨርተን በ46 ነጥብ ደረጃውን ከስምንተኛ ወደ ሰባተኛ ከፍ አድርጓል። ለአውሮፓ መድረክ ተሳትፎው ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቼልሲ በ48 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች የተሸነፈው ቼልሲ በሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ እያደረገ ባለው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥሏል።
በ3000 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ አትሌት ባለሽኝ ባወቀ እና አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ አራተኛና ስድስተኛ ወጥተዋል
Mar 21, 2026 95
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በ21ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ማምሻውን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የተሳተፉባቸው የፍጻሜ ውድድሮች ተደርገዋል። በ3000 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ አትሌት ባለሽኝ ባወቀ 9 ደቂቃ ከ00 ሴኮንድ ከ26 ማይክሮ ሴኮንድ አራተኛ ወጥታለች። በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊ አትሌት አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ 9 ደቂቃ ከ02 ሴኮንድ ከ41 ማይክሮ ሴኮንድ ስድስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ጣልያናዊቷ አትሌት ናዲያ ባቶክሌቲ 8 ደቂቃ ከ57 ሴኮንድ ከ64 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። አሜሪካዊቷ ኤሚሊ ማክካይ ሁለተኛ እና አውስትራሊያዊቷ ጄሲካ ሁል ሶስተኛ ደረጃን ይዘው ውድድራቸውን አጠናቀዋል። በወንዶች የ3000 ሜትር የፍጻሜ ውድድር አትሌት አዲሱ ይሁኔ 7 ደቂቃ ከ38 ሴኮንድ ከ60 ማይክሮ ሴኮንድ ስምንተኛ ወጥቷል። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ጌትነት ዋለ 7 ደቂቃ ከ40 ሴኮንድ ከ21 ማይክሮ ሴኮንድ 12ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። የታላቋ ብሪታኒያ አትሌት ጆሽ ኬር 7 ደቂቃ ከ35 ሴኮንድ ከ56 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል። አሜሪካዊው ኮል ሆከር ሁለተኛ ሲወጣ ፈረንሳዊው ያን ሽሩብ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። በፖላንድ ቶሩን ከተማ እየተካሄደ የሚገኘው 21ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል። ሻምፒዮናው ነገ ይጠናቀቃል።
ፉልሃም ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 21, 2026 94
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12 /2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ31ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ፉልሃም በርንሌይን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በክራቫን ኮቴጅ ስታዲየም ጆሽ ኪንግ እና ሃሪ ዊልሰን በጨዋታ ራውል ሂሚኔዝ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ዚያን ፍሌሚንግ ለበርንሌይ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ጋር አገናኝቷል። የበርንሌይ ጆሽ ላውረንት በ94ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ከሁለት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ፉልሃም በ44 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 19ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው በርንሌይ በ20 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በርንሌይ ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።
ሊቨርፑል በብራይተን ተሸነፈ
Mar 21, 2026 96
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 31ኛ ሳምንት ብራይተን ሊቨርፑልን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአሜክስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳኒ ዌልቤክ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። ሚሎስ ኬርኬዝ የሊቨርፑልን ብቸኛ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር የተደረገበት ሲሆን ለግብ የቀረቡ በርካታ ሙከራዎች ተደርገዋል። በሊጉ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው ብራይተን በ43 ነጥብ ደረጃውን ከ12ኛ ወደ 8ኛ ከፍ አድርጓል። ብራይተን በአውሮፓ መድረክ የመሳተፍ ተስፋውን ያለመለመ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሊቨርፑል በ49 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ቀያዮቹ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመግባት በሚያደርጉት ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥለዋል።
መቻል አራተኛ ተከታታይ ድሉን አስመዘገበ
Mar 21, 2026 69
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር መቻል ቦሌ ክፍለ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ በቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ትንቢት ሳሙኤል በ55ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። የመቻሏ አጥቂ ሴናፍ ዋቁማ በ88ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥታለች። ገነት ዮሐንስ ከመቻል የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው መቻል በ44 ነጥብ ደረጃውን ከአራተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ያሸነነፈው ጨዋታ ብዛት 13 ደርሷል። በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ31 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ የ20ኛ ሳምንት ጨዋታ ሲዳማ ቡና እና ድሬዳዋ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሲዳማ ቡና እና ድሬዳዋ ከተማ አቻ ተለያዩ
Mar 21, 2026 69
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት ሲዳማ እና ድሬዳዋ ከተማ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፊርማዬ ከበደ በ85ኛው ደቂቃ ባስቆጠረችው ጎል ድሬዳዋ ከተማ መሪ ሆኗል። ጨዋታው በድሬዳዋ ከተማ አሸናፊነት ተጠናቀቀ ሲባል ኤልሳቤጥ ብርሃኑ በ93ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈችው ግብ ለሲዳማ ቡና አንድ ነጥብ አስገኝቷል። ለሲዳማ ቡና ግቡን ያስቆጠረችው ኤልሳቤጥ ብርሃኑ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ማስመዝገብ አልቻለም። ድሬዳዋ ከተማ በ21 ነጥብ ከነበረበት ዘጠነኛ ደረጃ ወደ ስምንተኛ ከፍ ብሏል። ቡድኑ ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።
በ800 ሜትር ሴቶች ማጣሪያ አትሌት ንግስት ጌታቸው ለፍጻሜ አለፈች
Mar 21, 2026 71
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ 21ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና በፖላንድ ቶሩን ከተማ መካሄዱን ቀጥሏል። በ800 ሜትር ሴቶች ግማሽ ፍጻሜ ማጣሪያ በምድብ ሁለት የተወዳደረችው አትሌት ንግስት ጌታቸው 1 ደቂቃ ከ59 ሴኮንድ ከ46 ማይክሮ ሴኮንድ ሁለተኛ በመውጣት ለፍጻሜ አልፋለች። በሶስት ምድብ በተካሄደው የማጣሪያ ውድድር ከየምድቡ አንደኛ እና ሁለተኛ የወጡ አትሌቶች ለፍጻሜ አልፈዋል። የፍጻሜው ውድድር ነገ ምሽት 3 ሰዓት ከ53 ላይ ይካሄዳል።
በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉባቸው የፍጻሜ ውድድሮች ይካሄዳሉ
Mar 21, 2026 73
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በፖላንድ እየተካሄደ የሚገኘው 21ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል። ምሽት 3 ሰዓት ከ4 ደቂቃ ላይ የሴቶች የ3000 ሜትር የፍጻሜ ውድድር ይካሄዳል። ፍሬወይኒ ኃይሉ እና ባለሽኝ ባወቀ ኢትዮጵያን ወክለው ይወዳደራሉ። በውድድሩ ላይ 15 አትሌቶች ይሳተፋሉ። ምሽት 3 ሰዓት ከ22 ደቂቃ ላይ በሚካሄደው የ3000 ሜትር ወንዶች ፍጻሜ ጌትነት ዋለ እና አዲስ ይሁኔ የሚሳተፉ ይሆናል። ከፍጻሜው ውድድር በተጨማሪ ከቀኑ 8 ሰዓት ከ22 በ800 ሜትር ግማሽ ፍጻሜ ማጣሪያ አትሌት ንግስት ጌታቸው ትወዳደራለች። በሶስት ምድብ ተከፍሎ በሚደረገው ማጣሪያ ከእያንዳንዱ ምድብ አንደኛ እና ሁለተኛ የሚወጡ አትሌቶች ለፍጻሜው ያልፋሉ።
በፕሪሚየር ሊጉ መቻል ከቦሌ ክፍለ ከተማ ጋር ይጫወታል
Mar 21, 2026 83
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ መቻል ከቦሌ ክፍለ ከተማ በአበበ በቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቻል በሊጉ እስከ አሁን ያሸነፋቸው ጨዋታዎች ብዛት 12 ናቸው። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ አምስት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። በ19ኙ ጨዋታዎች ላይ 36 ግቦችን ሲያስቆጥር 11 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ41 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ካከናወናቸው 19 ጨዋታዎች መካከል ስምንቱን ያሸነፈው ቦሌ ክፍለ ከተማ በበኩሉ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሰባት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 23 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 18 ጎሎችን አስተናግዷል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ31 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። መቻል ካሸነፈ ተከታታይ አራተኛ ድሉን ያስመዘግባል። የሶስተኝነት ደረጃን ከሃዋሳ ከተማ ይረከባል። ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ያላሸነፈው ቦሌ ክፍለ ከተማ ወደ አሸናፊነት መንገድ ይመለሳል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ሲዳማ ቡና ከድሬዳዋ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና በሊጉ 19 ጨዋታዎች አድርጎ ስምንት ጊዜ ድል ሲቀናው በተመሳሳይ ስምንት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 19 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 24 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ27 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 19 ጨዋታዎች ስድስቱን ያሸነፈው ድሬዳዋ ከተማ በ11ዱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። በ19ኙ ጨዋታዎች 17 ግቦችን ሲያስቆጥር 30 ጎሎችን አስተናግዷል። ድሬዳዋ ከተማ በ20 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሲዳማ ቡና ካሸነፈ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። ባለፉት አራት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታል።
በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1500 አትሌት በርቄ ሐየሎም ወደ ፍፃሜ አለፈች
Mar 21, 2026 94
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 11/2018 (ኢዜአ)፦ 21ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ዛሬ በፖላንድ ቶሩን ተጀምሯል። በሴቶች 1500 ሜትር ማጣሪያ በምድብ ሁለት የተወዳደረችው አትሌት ብርቄ ሐየሎም 4 ደቂቃ 10 ሴኮንድ 66 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ ደረጃን በመያዝ ወደ ፍጻሜው አልፋለች። የሴቶች 1500 ሜትር ፍጻሜ ከነገ በስቲያ ይካሄዳል። በሴቶች 800 ሜትር ማጣሪያ በምድብ አራት ላይ የተወዳደረችው አትሌት ንግስት ጌታቸው በ2 ደቂቃ 02 ሴኮንድ 89 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት ለግማሽ ፍፃሜ አልፋለች። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በስድስት አትሌቶች ተወክላለች። ሻምፒዮናው እስከ መጋቢት 13 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
በፕሪሚየር ሊጉ ሊቨርፑል ከብራይተን ቼልሲ ከኤቨርተን ይጫወታሉ
Mar 21, 2026 113
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12 /2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 31ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ብራይተን ሊቨርፑልን በአሜክስ ስታዲየም ያስተናግዳል። ብራይተን በ40 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ሊቨርፑል በ49ኝ ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። በ30ኛ ሳምንት ሰንደርላንድ 1 ለ 0 ያሸነፈው ብራይተን ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ በአውሮፓ መድረክ የመሳተፍ ተስፋውን ያለመልማል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ያላሸነፈው ሊቨርፑል ማሸነፍ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኤቨርተን ከቼልሲ ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ በሂል ዲኪንሰን ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኤቨርተን በ43 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቼልሲ በ48 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በ30ኛ ሳምንት ኤቨርተን በአርሰናል፣ ቼልሲ በኒውካስትል ዩናይትድ ሽንፈት አስተናግደዋል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይፋለማሉ። ሶስት ነጥብ ለኤቨርተን በአውሮፓ መድረክ፣ ቼልሲ በሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በሚያደርጉት ፉክክር ወሳኝ የሚባል ነው። ፉልሃም ከበርንሌይ ምሽት 12 ሰዓት እና ሊድስ ዩናይትድ ከብሬንትፎርድ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
ማንችስተር ዩናይትድ ነጥብ ጥሏል
Mar 21, 2026 89
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/ 2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ31ኛ ሳምንት የመጀመሪያ መርሐ ግብር ቦርንማውዝ እና ማንችስተር ዩናይትድ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። በቫይታላቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ራያን ክሪስቲ በጨዋታ እና ጁኒየር ክሩፒ በፍጹም ቅጣት ምት ለቦርንማውዝ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ብሩኖ ፈርናንዴዝ በፍጹም ቅጣት ምት እና የቦርንማውዙ ጀምስ ሂል በራሱ ላይ ለዩናይትድ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። የማንችስተር ዩናይትዱ ተከላካይ ሃሪ ማጓየር በ78ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ጨዋታው ተመጣጣኝ እና አዝናኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ማጥቃት ላይ ያተኮረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በርካታ የግብ እድሎች ተፈጥረውበታል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ዩናይትድ በ55 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በሻምፒዮንስ ሊግ ፉክክሩ ወሳኝ ነጥብ ጥሏል። ቦርንማውዝ በ42 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሪነቱን አጠናክሯል
Mar 20, 2026 108
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 11/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ20ኛ ሳምንት ሶስተኛ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አዳማ ከተማን 6 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ረድኤት አስረሳኸኝ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርታለች። መሳይ ተመስገን ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ እሙሽ ዳንኤል ቀሪዋን ጎል ለንግድ ባንክ አስቆጥራለች። ሀትሪክ የሰራችው ረድኤት አስረሳኸኝ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጣለች። በሊጉ 17ኛ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነጥቡን ወደ 53 ከፍ በማድረግ መሪነቱን አጠናክሯል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ንግድ ባንክ ከተከታዩ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ያለው ልዩነት ወደ ሁለት ነጥብ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ በሊጉ ያስቆጠረችውን የግብ ብዛት ወደ 16 ከፍ በማድረግ 23 ግብ ያላትን የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞንን ትከተላለች። ዛሬ በተደረጉ የ20ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ሃዋሳ ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማን 1 ለ 0 ሲያሸንፍ ሸገር ከተማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሸገር ከተማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ነጥብ ተጋሩ
Mar 20, 2026 87
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት ሸገር ከተማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ማርታ ወልዴ በ23ኛው ደቂቃ ላይ ከመረብ ላይ ባሳረፈችው ግብ ሸገር ከተማ መሪ ሆኗል። የሸገር ከተማዋ ማህሌት ምትኩ በ90ኛው ደቂቃ ላይ በራሷ ላይ ያስቆጠረችው ጎል ለኢትዮ ኤሌክትሪክ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ቤተልሄም በቀለ በጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ ሸገር ከተማ በ39 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ51 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሁለት ተከታታይ የሊጉ ጨዋታዎች ነጥብ የጣለው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ከፍ ብሏል።
ሃዋሳ ከተማ ደረጃውን ወደ ሶስተኛ ከፍ ያደረገበት ድል አስመዘገበ
Mar 20, 2026 90
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። ረፋድ ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ፤ ሥራ ይርዳው በ62ኛው ደቂቃ ብቸኛውን ግብ አስቆጥራለች። ግቡን ያስቆጠረችው ሥራ ይርዳው የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ 12ኛ ድሉን ያስመዘገበው ሃዋሳ ከተማ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከአራተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ልደታ ክፍለ ከተማ በ15 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል።
በፕሪሚየር ሊጉ ማንችስተር ዩናይትድ ከቦርንማውዝ ጋር ይጫወታል
Mar 20, 2026 92
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 11/2018 (ኢዜአ):- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 31ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። ምሽት አምስት ሰዓት ላይ ቦርንማውዝ ከማንችስተር ዩናይትድ በቫይታሊቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቦርንማውዝ በ41 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ዩናይትድ በ54 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለሜዳው ቦርንማውዝ ባለፉት 10 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። በጨዋታዎቹ ላይ አራት ጊዜ ሲያሸንፍ ስድስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው ማንችስተር ዩናይትድ በጊዜያዊው አሰልጣኝ ማይክል ካሪክ እየተመራ ጠንካራ ግስጋሴ እያደረገ ነው። ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። ቦርንማውዝ በአውሮፓ መድረክ የመሳተፍ ህልሙን ለማስቀጠል ይፋለማል። በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ እየተፎካከረ የሚገኘው ማንችስተር ዩናይትድ ሶስት ነጥብ ማግኘት ወሳኝ ነው። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ43 ዓመቱ ስቱዋርት አትዌል ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 31ኛ ሳምንት እስከ መጋቢት 13 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ20ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታዎች
Mar 20, 2026 68
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 11/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። በዕለቱ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከረፋዱ 9 ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዳማ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው 19 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ሲያሸንፍ በስምንቱ ተሸንፏል። በስድስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። በ19ኙ ጨዋታዎች ላይ 14 ግቦችን ሲያስቆጥር 28 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ21 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በበኩሉ በውድድር ዓመቱ 19 ጨዋታዎችን አድርጎ 16 ጊዜ ድል ሲቀናው የተሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። 52 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ሰባት ጎሎችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ50 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ንግድ ባንክ በሊጉ በርካታ ግቦችን ያስቆጠረ እና አነስተኛ የጎል መጠን ያስተናገደ ቡድን ነው። በ19ኛ ሳምንት ከቦሌ ክፍለ ከተማ አንድ አቻ የተለያየው አዳማ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። በሌላኛው መርሐ- ግብር ሸገር ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ከቀኑ 7 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሸገር ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው 19 ጨዋታዎች 12 ጊዜ ሲያሸንፍ አምስተኛ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በ19ኙ ጨዋታዎች ላይ 32 ግቦችን ሲያሳርፍ 19 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ38 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ 19 ጨዋታዎችን አድርጎ በ16ቱ አሸንፎ በአንዱ ተሸንፎ በሁለቱ አቻ ወጥቷል። 43 ግቦችን ሲያስቆጥር 10 ጎሎች ገብተውበታል። ቡድኑ በ50 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በ19ኛ ሳምንት ከድሬዳዋ ከተማ ጋር አንድ አቻ የወጣው ሸገር ከተማ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ19ኛ ሳምንት ከሃዋሳ ከተማ ጋር ያለ ግብ አቻ መለያየቱን ተከትሎ የሊጉን መሪነት ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አስረክቧል። ማሸነፍ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ እንዲያገኝ ያስችለዋል። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ሃዋሳ ከተማ ከልደታ ክፍለ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታውን ያደርጋል። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ 19 ጨዋታዎችን በማድረግ 11ዱን ሲያሸንፍ በሁለቱ ተሸንፏል። ስድስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 33 ግቦችን ሲያስቆጥር 12 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ39 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ልደታ ክፍለ ከተማ በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው 19 ጨዋታዎች በአራቱ ድል ሲቀናው 12 ጊዜ ተሸንፏል። በሶስቱ ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። 21 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 39 ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ15 ነጥብ 10ኛ ላይ ተቀምጧል። በ19ኛ ሳምንት ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ያለ ግብ አቻ የተለያየው ሃዋሳ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ልደታ ክፍለ ከተማ ካሸነፈ ወደ ድል መንገድ ይመለሳል። የዛሬ ጨዋታዎች በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ የሚባሉ ናቸው። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት እስከ መጋቢት 13 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን በ22 ግቦች እየመራች ነው። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ በ13 ጎሎች ትከተላለች።
21ኛ የዓለም የቤት ውስጥ ዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ይጀመራል
Mar 20, 2026 75
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 11/2018 (ኢዜአ)፦ 21ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ (World Athletics Indoor Championship) ዛሬ በፖላንድ ቶሩን ከተማ ይጀመራል። በውድድሩ ላይ ከ118 ሀገራት የተወጣጡ 674 አትሌቶች ይሳተፋሉ። ከነዚህም ውስጥ 345 ወንድ እና 329 ሴት አትሌቶች ናቸው። ኢትዮጵያም በሻምፒዮናው ላይ በስድስት አትሌቶች እንደምትወከል የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ብርቄ ኃየሎም፣ ጌትነት ዋለ፣ ንግስት ጌታቸው፣ ፍሬወይኒ ኃይሉ፣ ባለሽኝ ባወቀ እና አዲስ ይሁኔ ናቸው። አትሌቶቹ በ800 እና 3000 ሜትር ውድድሮች ላይ ይሳተፋሉ። የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን ከአትሌቶቹ በተጨማሪ አንድ ቡድን መሪ፣አንድ የቴክኒክ ቡድን መሪ እና አንድ አሰልጣኝ አካቷል። ሻምፒዮናው እስከ መጋቢት 13 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን በሁለቱም ጾታዎች በተመሳሳይ 13 በድምሩ 26 የወርቅ ሜዳሊያ የሚያስገኙ ውድድሮች ይካሄዳሉ። በ20ኛው የዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳሊያ ያገኙ አትሌቶች ድላቸውን ለማስጠበቅ በዘንድሮ ውድድር ላይ ይሳተፋሉ። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2025 በቻይና ናንጂንግ በተካሄደው 20ኛው የዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሁለት የወርቅ እና ሶስት የብር በድምሩ አምስት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ላይ ስትሳተፍ የአሁኑ ለ19ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም በነበራት 18 ተሳትፎዎቿ 35 የወርቅ ፣ 17 የብር እና 15 የነሐስ በአጠቃላይ 67 ሜዳሊያዎችን አግኝታለች።
የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በአውሮፓ እግር ኳስ ውድድር ላይ ይሳተፋል
Mar 19, 2026 131
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 10/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ባዘጋጀው የወዳጅነት ውድድር ላይ እንደሚሳተፍ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታወቀ። የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር የሚያካሂደው የ"UEFA Frendship Cup" ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ውድድር በቱርክዬ አስተናጋጅነት ከመጋቢት 28 እስከ ሚያዝያ 10 ይከናወናል። በዚህ ውድድር ላይ ከተለያዩ አህጉራት የተውጣጡ ሀገራት የሚሳተፉ ሲሆን፤ የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ጋር በፈጠረው ግንኙነት ከአፍሪካ ከሚሳተፉ ሁለት ሀገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ መሆን ችላለች። በዚህም ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ተሳታፊ እንደሚሆን መረጋገጡን ፌዴሬሽኑ ጠቁሟል። በዚህ ውድድር ላይ አስተናጋጇ ቱርክዬን ጨምሮ ኢትዮጵያ፣ ኖርዌይ፣ ኡዝቤኪስታን፣ ኮስታሪካ፣ ፓራጓይ፣ ዩራጓይ እና ሞሮኮ ይሳተፋሉሉ።
አራተኛ ቀኑን የያዘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዝግጅት
Mar 19, 2026 115
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 10/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታዋን ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ታደርጋለች። ለማጣሪያው በአሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ጥሪ የተደረገላቸው ተጫዋቾች ከመጋቢት 7 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ዝግጅታችውን ማድረግ ቀጥለዋል። ቡድኑ የአራተኛ ቀን ልምምዱን ዛሬ በአዲስ አበባ ስታዲየም ማድረጉን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ጋቶች ፓኖም (አል ዓረቢ ሳዑዲ ዓረቢያ) እና ከነዓን ማርክነህ ( አል ሻባብ ኦማን) ብሔራዊ ቡድኑን በመቀላቀል ልምምድ ማድረግ ጀምረዋል። ኢትዮጵያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር የማጣሪያ ጨዋታዎቿን መጋቢት 18 እና 22 ቀን 2018 ዓ.ም ታደርጋለች።