ቀጥታ፡
ስፖርት
የዓለም ዋንጫ ሁለተኛ ዙር ጨዋታ፤ ሴኔጋል ከኖርዌይ፡አልጄሪያ ከጆርዳን
Jun 22, 2026 176
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የምድብ 9 እና 10 ሁለተኛ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። በምድብ ዘጠኝ ኖርዌይ ከሴኔጋል በኒው ዮርክ ኒው ጀርዚ ስታዲየም ከሌሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ ኖርዌይ ኢራቅን 3 ለ 1 ስትረታ ሴኔጋል በፈረንሳይ 3 ለ 1 ተሸንፋለች። ኖርዌይ ካሸነፈች ጥሎ ማለፍ መግባቷን ታረጋግጣለች። የምዕራብ አፍሪካዋ ሴኔጋል ወደ ቀጣዩ ዙር የማለፍ ህልሟን እውን ለማድረግ ከጨዋታው ሶስት ነጥብ ማግኘት ይጠበቅባታል። በዚሁ ምድብ ፈረንሳይ ከኢራቅ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ላይ በፊላደልፊያ ስታዲየም ይጫወታሉ። የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት ያገኘችው ፈረንሳይ ድል ከቀናት ወደ ጥሎ ማለፉ ትገባለች። ኢራቅ በውድድሩ ላይ ለመቆየት ከጠንካራዋ ፈረንሳይ ሶስት ነጥብ ማግኘት ይጠበቅባታል። በምድብ 10 ጆርዳን ከአልጄሪያ ከጠዋቱ 12 ሰዓት ላይ በሳንፍራንሲስኮ ቤይ ኤሪያ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። በመጀመሪያው የምድብ ጨዋታቸው ጆርዳን በኦስትሪያ 3 ለ 1፣ አልጄሪያ በአርጀንቲና የ3 ለ 0 ሽንፈት አስተናግደዋል። ሁለቱ ቡድኖች የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይፋለማሉ። አሸናፊው ቡድን ወደ ጥሎ ማለፍ የመግባት ተስፋውን ያለመልማል። በዚሁ ምድብ አርጀንቲና ከኦስትሪያ ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ በዳላስ ስታዲየም ይጫወታሉ። የመጀመሪያ የምድብ ጨዋታቸውን ያሸነፉት ሁለት ሀገራት የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል። ጨዋታውን የሚያሸንፈው ሀገር ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቱን ያረጋግጣል።
ከአውሮፓ እና ደቡብ አሜሪካ እጅ ወጥቶ የማያውቀው የዓለም ዋንጫ ክብር
Jun 22, 2026 145
በሙሴ መለሰ እግር ኳስ በዓለም ላይ ተወዳጅ ከሆኑ ስፖርቶች መካከል አንዱ ነው። በየአራት ዓመቱ የሚካሄደው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የእግር ኳስ አፍቃሪያን ትኩረት የሚስብ ግዙፍ ውድድር መሆኑ ይታወቃል። የዓለም ዋንጫ ትልቁ ስፖርታዊ ሁነት ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም። ይህ ግዙፍ ሁነት መካሄድ ከጀመረ አንድ ክፍለ ዘመን ሊያስቆጥር ነው። እ.አ.አ በ1930 የመጀመሪያው ዓለም ዋንጫ ኡራጓይ አስተናጋጅነት ተከናውኗል። በወቅቱ አዘጋጇ ሀገር አርጀንቲናን በመርታት ታሪካዊውን ዋንጫ አንስታለች። እስከ አሁን በተደረጉ 22 የዓለም ዋንጫዎች 80 ሀገራት የተሳተፉ ሲሆን ከነዚህ ውሰጥ ዋንጫ ማንሳት የቻሉት ስምንት ሀገራት ብቻ ናቸው። ብራዚል፣ ጀርመን፣ ጣልያን፣ አርጀንቲና፣ ፈረንሳይ፣ ኡራጓይ፣ እንግሊዝ እና ስፔን ዋንጫውን ያነሱ ሀገራት ናቸው። በውድድሩ የ96 ዓመታት ታሪክ ውስጥ ዋንጫው ከአውሮፓ እና ደቡብ አሜሪካ ሀገራት እጅ ወጥቶ አያውቅም።   ከዚህም ባለፈ በነዚህ አህጉራት ከሚገኙ ሀገራት ውጪ ለፍጻሜ አልፎ የሚያልቅ ብሔራዊ ቡድን አለመኖሩ ሌላኛው ትኩረት የሚስብ ጉዳይ ነው። ከ22ቱ የዓለም ዋንጫዎች 12ቱ ወደ አውሮፓ ሀገራት አምርተዋል። የደቡብ አሜሪካ ሀገራት 10 ጊዜ ዋንጫውን አንስተዋል። ብራዚል አምስት ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት ስኬታማዋ ሀገር ናት። ጀርመን እና ጣልያን በተመሳሳይ አራት ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ ይከተላሉ። አርጀንቲና ሶስት ጊዜ ዋንጫውን ማንሳት ችላለች። የወቅቱም የውድድሩ አሸናፊ ናት። ፈረንሳይ እና ኡራጓይ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ ዋንጫውን አንስተዋል። እንግሊዝ እና ስፔን በተመሳሳይ አንድ ጊዜ የዋንጫ ባለቤት ሆነዋል። በዓለም ዋንጫው ከሰባት አህጉራት የተወጣጡ ሀገራት እየተሳተፉ ቢገኝም አሸናፊነቱ ከአውሮፓ እና ደቡብ አሜሪካ አለመውጣቱ የሁለቱን አህጉራት ፍጹም የበላይነት የሚያሳይ ነው። 23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በአሜሪካ፣ ሜክሲኮ እና ካናዳ ጣምራ አዘጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። በውድድሩ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ 48 ሀገራት እየተሳተፉ ይገኛል። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ አሸናፊ ከደቡብ አሜሪካ እና አውሮፓ ሀገራት ወጥቶ የሌላ አህጉር ቡድን ያሸነፍ ይሆን? የሚለው ጉዳይ ትኩረትን ስቧል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 36ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
Jun 22, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 36ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ፋሲል ከነማ ከአርባምንጭ ከተማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። በ35ኛው ሳምንት ሀዲያ ሆሳዕናን 1 ለ 0 የረታው ፋሲል ከነማ በ49 ነጥብ ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አርባምንጭ ከተማ በ35 ነጥብ 20ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ተከታታይ ጨዋታዎች ድል አስመዝግቧል። ጨዋታው ፋሲል ከነማ በድል ጉዞው ለመቀጠል አርባምንጭ ከተማ ከመውረድ ለመትረፍ እያደረገው ባለው ጉዞ ሶስት ነጥብ ለማግኘት የሚያደርጉት ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ወላይታ ድቻ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ወላይታ ድቻ በ47 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በተመሳሳይ 47 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ35ኛ ሳምንት ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 ያሸነፈው ወላይታ ድቻ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። በአንጻሩ ባለፉት አራት ጨዋታዎች ማሸነፍ ያልቻለው ኢትዮ ኤሌክትሪክ የድልን መንገድን ለማግኘት ይፋለማል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሀዲያ ሆሳዕና ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባለፉት ሶስት የሊጉ ጨዋታዎች አቻ የተለያየው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ42 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ሀዲያ ሆሳዕና በ43 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ካለፉት ሶስት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ማግኘት አልቻለም። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚጫወቱ ሲሆን ሶስት ነጥብ የሚያገኘው ቡድን በሊጉ መቆየቱን የሚያረጋግጥበት እድል ሊኖር ይችላል። በተያያዘም ትናንት በመብራት ምክንያት ተቋርጦ የነበረው የቅዱስ ጊዮርጊስ እና ምድረ ገነት ሽሬ መርሐ ግብር ቀሪ ስድስት ደቂቃ ከረፋዱ አራት ሰዓት አንስቶ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋል። ጨዋታው እስከተቋረጠበት ጊዜ ድረስ ግብ አልተቆጠረም።
ኬፕቨርዴ ከኡራጓይ ጋር አቻ ተለያየች
Jun 22, 2026 130
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ኬፕቨርዴ እና ኡራጓይ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ከእኩለ ሌሊት በኋላ በሚያሚ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ የምድብ ሰባት ጨዋታ ኬቨን ፒና እና ሄሊዮ ቫሬላ የኬፕቨርዴን ጎሎች አስቆጥረዋል። ፒና በዓለም ዋንጫ ለመጀመሪያ ጊዜ እየተሳተፈች ለምትገኘው አፍሪካዊቷ ኬፕቨርዴ በውድድሩ የመጀመሪያ ግቧን በማስቆጠር ታሪክ ሰርቷል። የደሴቲቷ ሀገር ከስፔን ጋር በመጀመሪያ ጨዋታዋ ያለ ግብ አቻ ተለያይታ የመጀመሪያ ነጥቧን ማግኘቷ የሚታወስ ነው። ማክሲ አራውጆ እና ኦግስቲን ካኖቢዮ የኡራጓይን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ኬፕቨርዴ የግብ እድሎችን በመፍጠር፣ ኡራጓይ በኳስ ቁጥጥር የተሻሉ ነበሩ። የኬፕቨርዴው ኬቨን ፒና የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ ኡራጓይ እና ኬፕቨርዴ በተመሳሳይ ሁለት ነጥብ በግብ ልዩነት ተበላልጠው ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ትናንት ማምሻውን በምድብ ስምንት በተካሄደ ጨዋታ ስፔን ሳዑዲ አረቢያን 4 ለ 0 በማሸነፍ ምድቡን በአራት ነጥብ እየመራች ነው። በምድብ ስምንት የመጨረሻ መርሐ ግብር ኬፕቨርዴ ከሳዑዲ አረቢያ እና ኡራጓይ ከስፔን ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
መቻል ድል ቀንቶታል
Jun 21, 2026 557
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 14/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ36ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ጨዋታ መቻል ኢትዮጵያ መድንን 1 ለ 0 አሸንፏል። መሐመድ አበራ በ61ኛው ደቂቃ ግቧን አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ መቻል በ56 ነጥብ ሶስተኛ፣ ኢትዮጵያ መድን በ46 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዘዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ እና አዳማ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። መቀሌ 70 እንደርታ በ37 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። አዳማ ከተማ በ43 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም እየተደረገ የነበረው የምድረ ገነት ሽሬ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ጨዋታ በ90ኛው ደቂቃ መብራት በመጥፋቱ ምክንያት ተቋርጧል። ጨዋታው እስከተቋረጠበት ጊዜ ግብ አልተቆጠረም። ቀሪው ስድስት ደቂቃ ነገ ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ እንደሚካሄድ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል። በዕለቱ የመጀመሪያ መርሐ ግብር ሃዋሳ ከተማ እና ባህር ዳር ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተካሄዷል። ውጤቱን ተከትሎ ሃዋሳ ከተማ በ49 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ባህር ዳር ከተማ በ47 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በበርካታ ጨዋታዎች አቻ የወጣ (20 ጊዜ) የወጣ ቡድን ነው።
ግብጽ ከኒውዝላንድ ኬፕቨርዴ ከኡራጓይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ
Jun 21, 2026 370
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 14/2018 (ኢዜአ)፦ በአሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ ጣምራ አዘጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ዛሬ 12ኛ ቀኑን ይዟል። በምድብ ሰባት ኒውዝላንድ ከግብጽ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ በቢሲ ፕሌስ ስታዲየም ይጫወታሉ። በምድቡ በተደረጉ የመጀመሪያ ጨዋታዎች ኒውዝላንድ ከኢራን ሁለት አቻ ስትለያይ፣ ግብጽ ከቤልጂየም አንድ አቻ ወጥታለች። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫው የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። አፍሪካዊቷ ግብጽ ማሸነፍ ጥሎ ማለፍ የመግባት እድሏን ያሰፋል። በዚሁ ምድብ ቤልጂየም ከኢራን ምሽት አራት ሰዓት ላይ በሎስ አንጀለስ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የመክፈቻ ጨዋታቸውን በአቻ ውጤት ያጠናቀቁት ሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች፣ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ብርቱ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በተያያዘም በምድብ ስምንት ኡራጓይ ከኬፕቨርዴ ነገ ከጠዋቱ አንድ ሰዓት በሚያሚ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አፍሪካዊቷ ሀገር ኬፕቨርዴ በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታዋ ከስፔን ጋር ያለ ግብ አቻ በመለያየት የዓለም መነጋገሪያ ሆናለች። በዓለም ዋንጫ ለመጀመሪያ ጊዜ በውድድሩ ላይ እየተሳተፈች የምትገኘው ኬፕቨርዴ በጥሩ ተነሳሽነት ላይ ትገኛለች። ከ500 ሺህ በላይ ህዝብ ያላት ኬፕቨርዴ ማሸነፍ ከቻለች ወደ ጥሎ ማለፍ የመግባት እድሏ ሰፊ ይሆናል። በመጀመሪያ ጨዋታዋ ሳዑዲ አረቢያ ጋር አንድ አቻ የተለያየችው ኡሯጓይ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ትጫወታለች። በዚሁ ምድብ ስፔን ከሳዑዲ አረቢያ ከምሽቱ አንድ ሰዓት በአትላንታ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሁለቱም ሀገራት በውድድሩ ላይ የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይፋለማሉ።
በሊጉ የ36ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ
Jun 21, 2026 210
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 14/ 2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 36ኛ ሳምንት ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ መቻል ከኢትዮጵያ መድን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። መቻል በ53 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ መድን በ46 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ድል ያልቀናው መቻል የአሸናፊነትን መንገድ ለማግኘት ይጫወታል። በ35ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ድሬዳዋ ከተማን 1 ለ 0 የረታው ኢትዮጵያ መድን ካሸነፈ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። መድን የአምና የሊጉ አሸናፊ እንደነበር ይታወሳል። በሌላኛው መርሐ ግብር ምድረ ገነት ሽሬ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረ ገነት ሽሬ በ37 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ49 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ምድረ ገነት ሽሬ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ትግል ጨዋታውን ማሸነፍ ይኖርበታል። በጥሩ ወቅታዊ ብቃት ላይ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ሌላኛው የዕለቱ መርሐ ግብር ሃዋሳ ከተማ እና ባህር ዳር ከተማን ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ያገናኛል። ሃዋሳ ከተማ በ48 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በ46 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። በ35ኛ ሳምንት በነገሌ አርሲ 2 ለ 1 የተሸነፈው ሃዋሳ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይፋለማል። ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ባህር ዳር ከተማ የድል መንገዱን ለማግኘት ይፋለማል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በበርካታ ጨዋታዎች (19 ጊዜ) አቻ የወጣ ቡድን ነው። ከቀኑ 10 ሰዓት መቀሌ 70 እንደርታ ከአዳማ ከተማ በአበባ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቀሌ 70 እንደርታ በ36 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። አዳማ ከተማ በ42 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ተከታታይ ጨዋታዎች አቻ የወጣው መቀሌ 70 እንደርታ በሊጉ የመቆየት ተስፋውን ለማለምለም ሶስት ነጥብ ማግኘት ይጠበቅበታል። በ35ኛ ሳምንት ኢትዮዮጵያ ንግድ ባንክን 2 ለ 1 የረታው አዳማ ከተማ ዛሬ ካሸነፈ በሊጉ የመቆየት እድሉን ይበልጥ ያሰፋል። ጨዋታው ላለመውረድ እየተደረገ ባለው ፉክክር ትልቅ ትርጉም የሚሰጠው ነው።
ቱኒዚያ ከዓለም ዋንጫው ተሰናበተች
Jun 21, 2026 215
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 14/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ ስድስት መርሐ ግብር ጃፓን ቱኒዚያን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፋለች። ማለዳ ላይ በሞንቴሬይ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አያሴ ኡዳ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ዳይቺ ካማዳ እና ጁንያ ኢቶ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ካማዳ በዓለም ዋንጫው 1000ኛ ጨዋታ የመጀመሪያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ጃፓን በተጋጣሚዋ ላይ የተሻለ ብልጫ ነበራት። በአንጻሩ ቱኒዚያ ደካማ የጨዋታ እንቅስቃሴ አድርጋለች። 1000ኛውን የዓለም ዋንጫ ጨዋታ የዓለም አቀፉ እግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ እና የጃፓን ልዕልት ሂሳኮ በስታዲየም በመገኘት ተከታትለውታል። በውድድሩ ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ቱኒዚያ ከዓለም ዋንጫው የተሰናበተች ሶስተኛ ሀገር ሆናለች። ቱኒዚያ በስዊድን የ5 ለ 1 ሽንፈት ካስተናገደች በኋላ አሰልጣኝ ሳብሪ ላሙቺን በማሰናበት የቀጠረቻቸው ፈረንሳዊ አሰልጣኝ ሀርቬ ሬናርድ በመጀመሪያ ጨዋታቸው ሽንፈት አስተናግደዋል። ቱርኪዬ እና ሀይቲ ሌሎች ከዓለም ዋንጫው መሰናበታቸውን ያረጋገጡ ሀገራት ናቸው። ድል የቀናት ጃፓን በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ምድብ ትናንት ማምሻውን በተደረገ ጨዋታ ኔዘርላንድስ ስዊድንን 5 ለ 1 አሸንፋለች። በመጨረሻው የምድቡ መርሐ ግብር ቱኒዚያ ከኔዘርላንድስ፣ ጃፓን ከስዊድን ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ሲዳማ ቡና በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የሊጉ ሻምፒዮን ሆነ
Jun 20, 2026 633
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 13/ 2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ36ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ከነገሌ አርሲ ጋር አንድ አቻ በመለያየት የሊጉን ዋንጫ ማንሳቱን አረጋግጧል። ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያን ወክሎ በቀጣዩ ዓመት በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ይሳተፋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ብርሃኑ በቀለ በመጀመሪያ አጋማሽ ማብቂያ ላይ ያስቆጠረው ጎል ሲዳማ ቡናን መሪ አድርጓል። በረከት ወልዴ በ76ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ ባሳረፈው ጎል ነገሌ አርሲ አቻ ሆኗል። የነገሌ አርሲው ቦና ቦካ በ16ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ውጤቱን ተከትሎ ሲዳማ ቡና በ65 ነጥብ ሁለት ጨዋታ እየቀረው ለመጀመሪያ ጊዜ የሊጉን ዋንጫ ማንሳቱን አረጋግጧል። ቡድኑ በውድድር ዓመቱ ከሌሎች ተፎካካሪዎቹ በአንጻራዊነት ወጥነት ያለው አቋም ያሳየ ሲሆን ለበርካታ ሳምንታትም የሊጉ መሪ ሆኖ ቆይቷል። ሲዳማ ቡና ሻምፒዮን መሆኑን ተከትሎ ኢትዮጵያን ወክሎ በቀጣይ ዓመት በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ይሳተፋል። በሌላ በኩል ሲዳማ ቡና ሰኔ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር የኢትዮጵያ ዋንጫን ለማንሳት ይፋልማል። ቡድኑ ዓመቱን በሁለት ዋንጫ የማጠናቀቅ እድል አለው። ነገሌ አርሲ በ57 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ድሬዳዋ ከተማ ሸገር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። አብዲሳ ጀማል በ19ኛው እና አብዱልሰላም ዩሱፍ በ84ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ከዘጠኝ የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ድሬዳዋ ከተማ በ38 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ላለመውረድ በሚያደርገው ትግል ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በሊጉም ስምንተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሸገር ከተማ በ44 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረገ የ36ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮጵያ ቡና ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የ36ኛ ሳምንት መርሐ ግብር እስከ ሰኔ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
መንግስት ለስፖርት ዘርፉ በሰጠው ከፍተኛ ትኩረት አበረታች ስኬቶች ተመዝግበዋል
Jun 20, 2026 828
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 13/2018 (ኢዜአ)፦መንግስት ለስፖርት ዘርፉ በሰጠው ከፍተኛ ትኩረት አበረታች ስኬቶች መመዝገባቸውን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወርቀሰሙ ማሞ ገለጹ። የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር በስፖርት ልማት ዘርፍ ዙሪያ ከክልሎች፣ ከተማ አስተዳደሮችና ከባለድርሻ አካላት ጋር የውይይት መድረክ እያካሄደ ይገኛል።   በመድረኩ ላይ የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ወይዘሮ ወርቀሰሙ ማሞ፣ የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ ታደለ ቡራቃ (ዶ/ር) ፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ፣ ሚኒስትር ዴኤታዎችና የተለያዩ የዘርፉ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወርቀሰሙ ማሞ በዚሁ ወቅት፤ የስፖርት ዘርፍ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ ስሟ ከፍ ብሎ እንዲጠራ ማድረግ አስችሏል ብለዋል፡፡ በአካልና የአእምሮ ብቁ የሆነ ትውልድን በመቅረጽና በመገንባት ረገድ የማይተካ ሚና እንዳለው ጠቁመው ይህንን ድርሻውን እየተወጣ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል። ዘርፉን ዘመኑን በዋጀ አሰራርና ሕግ ለመምራት የፖሊሲና የአዋጅ ማሻሻያ ስራዎች መከናወናቸውን የጠቀሱት ሰብሳቢዋ፤ መንግስት ለስፖርቱ ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረትና በገባው ቃል መሰረት በተሰሩ የተቀናጁ ተግባራት አመርቂ ለውጥ መመዝገቡን ገልጸዋል። በተለይም ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራትና የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን በስፋት ተደራሽ በማድረግ ረገድ ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸውን አብራርተዋል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ በበኩላቸው፤ በስፖርት ዘርፍ ማዘውተሪያ ስፍራዎች ግንባታና በሌሎችም የስፖርት ወርቃማ ጊዜ ላይ እንገኛለን ብለዋል።   በመላ ሀገሪቱ ከ45 ሺህ በላይ፣ በአዲስ አበባ ከተማ ደግሞ ከ2 ሺህ 500 በላይ የሚሆኑ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ተገንብተው ለሕዝቡ ክፍት መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የተገነቡት መሰረተ ልማቶች ሀገሪቱ ዓለም አቀፍና አህጉራዊ ውድድሮችን በብቃት እንድታስተናግድ ትልቅ አቅም መፍጠራቸውን ጠቁመዋል፡፡ በስፖርት ልማትና በስፖርት ዲፕሎማሲ ዘርፍ የተጀመሩ ስኬታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
በዓለም ዋንጫው ኮትዲቯር ከጀርመን የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል
Jun 20, 2026 395
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 13/2018 (ኢዜአ):- በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የምድብ አምስት መርሐ ግብር ኮትዲቯር ከጀርመን ጋር ዛሬ ጨዋታዋን ታከናውናለች። ጨዋታው ከምሽቱ አምስት ሰዓት ላይ በቶሮንቶ ስታዲየም ይከናወናል። የምዕራብ አፍሪካዋ ኮትዲቯር በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታዋ ኢኳዶርን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ይህም በዘንድሮው ዓለም ዋንጫ ድል የቀናት የመጀመሪያ አፍሪካዊ ሀገር እንድትሆን አስችሏታል። የአራት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊ ጀርመን በመጀመሪያ ጨዋታዋ ኩራሳኦን 7 ለ 1 ረምርማለች። ጀርመን ጨዋታውን የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት ብታገኝም ኮትዲቯር ጠንካራ ፉክክር ታደርጋለች ተብሎ ይጠበቃል። አሸናፊ ቡድን ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቱን ያረጋግጣል። በዚሁ ምድብ ኢኳዶር ከኩራሳኦ በካንሳስ ሲቲ ስታዲየም ከሌሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በመጀመሪያ ጨዋታቸው ሽንፈት ያስተናገዱት ሁለቱ ሀገራት ድል ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። በተያያዘም የምድብ ስድስት ሁለተኛ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ኔዘርላንድስ ከስዊድን ከምሽቱ ሁለት ሰዓት በሂውስተን ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በመጀመሪያ ጨዋታ ኔዘርላንድስ ከጃፓን ጋር ሁለት አቻ ስትለያይ ስዊድን ቱኒዚያን 5 ለ 1 አሸንፋለች። ኔዘርላንድስ ወደ ጥሎ ማለፍ የመግባት እድሏን ለማስፋት ማሸነፍ ይጠበቅባታል። ተጋጣሚዋ ስዊድን ካሸነፈች ወደ ጥሎ ማለፍ ትገባለች። በዚሁ ምድብ ቱኒዚያ ከጃፓን ከጠዋቱ አንድ ሰዓት ላይ በሞንቴሬይ ስታዲየም ይጫወታሉ። በመጀመሪያ ጨዋታው ሽንፈት ያስተናገደችው ቱኒዚያ በውድድሩ ላይ ለመቆየት ጨዋታውን ማሸነፍ ግድ ይላታል። አንድ ነጥብ ያላት ጃፓን ማሸነፍ ጥሎ ማለፍ የመግባት እድሏን ያሰፋላታል።
ሲዳማ ቡና የሊጉን አሸናፊነት ለማረጋገጥ ከነገሌ አርሲ ጋር ወሳኝ ጨዋታ ያደርጋል
Jun 20, 2026 256
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 13/ 2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 36ኛ ሳምንት ዛሬ በሚደረጉ አራት ጨዋታዎች ጅማሮውን ያገኛል። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ሲዳማ ቡና ከነገሌ አርሲ በአዲስ አበባ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል። ሲዳማ ቡና በ64 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ነገሌ አርሲ በ56 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሶስት ተከታታይ ጨዋታዎች ድል የቀናው ሲዳማ ቡና በዛሬው መርሐ ግብር ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የሊጉን ዋንጫ ማንሳቱን ያረጋግጣል። በ35ኛ ሳምንት ሃዋሳ ከተማን 2 ለ 1 ያሸነፈው ነገሌ አርሲ ዋንጫውን ለማንሳት ያለውን ጭላንጭል ተስፋ ለማስቀጠል የግድ ማሸነፍ ይኖርበታል። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያ ዙር በ17ኛ ሳምንት ባደረጉት ጨዋታ ነገሌ አርሲ ዳዊት ተፈራ በፍጹም ቅጣት ምት ባስቆጠረው ጎል 1 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ምድረ ገነት ሽሬ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረ ገነት ሽሬ በ37 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ49 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ምድረ ገነት ሽሬ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ትግል ጨዋታውን ማሸነፍ ይኖርበታል። በጥሩ ወቅታዊ ብቃት ላይ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከኢትዮጵያ ቡና በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ45 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ቡና በ46 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ35ኛ ሳምንት በአዳማ ከተማ የ2 ለ 1 ሽንፈት ያስተናገደው ንግድ ባንክ ወደ ድል መንገድ ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። ባለፉት ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎች የተሸነፈው ኢትዮጵያ ቡና ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይፋለማል። ፋሲል ከነማ ከአርባምንጭ ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። በ35ኛው ሳምንት ሀዲያ ሆሳዕናን 1 ለ 0 የረታው ፋሲል ከነማ በ49 ነጥብ ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አርባምንጭ ከተማ በ35 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ተከታታይ ጨዋታዎች ድል አስመዝግቧል። ጨዋታው ፋሲል ከነማ በድል ጉዞው ለመቀጠል አርባምንጭ ከተማ ከመውረድ ለመትረፍ እያደረገው ባለው ጉዞ ሶስት ነጥብ ለማግኘት የሚያደርጉት ነው። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 36ኛ ሳምንት እስከ ሰኔ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ ናትናኤል ዳንኤል በተመሳሳይ 14 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በጋራ እየመሩ ነው። የፋሲል ከነማው ታምራት እያሱ በ12 እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ አዲስ ግደይ በ11 ግቦች ይከተላሉ።
ፓራጓይ ወሳኝ ድል ተቀዳጅታለች
Jun 20, 2026 221
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ አራት መርሐ ግብር ፓራጓይ ቱርኪዬን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማለዳ ላይ በሳንፍራንሲስኮ ቤይ ኤሪያ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ማቲያስ ጋላርዛ በ64ኛው ሴኮንድ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ጎሉ የዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ፈጣን ጎል ሆኖ ተመዝግቧል። በመጀመሪያው አጋማሽ ማብቂያ የፓራጓይ የአማካይ ተጫዋች ሚጉዌል አልሚሮን በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። አልሚሮን አፉን በእጅ ሸፍኖ የተቃራኒ ቡድን ተጫዋች በመናገሩ ቀይ ካርድ ተመልክቷል። ይህም የ32 ዓመቱ አማካይ አፍን በእጅ ሸፍኖ መናገር ቀይ ካይ ካርድ የሚያሰጥበት አዲሱ የፊፋ ህግ ተግባራዊ የሆነበት የመጀመሪያው ተጫዋች ሆኗል። ቱርኪዬ ያገኘችውን የቁጥር ብልጫ ተጠቅማ ግብ ማስቆጠር አልቻለችም። ውጤቱን ተከትሎ ፓራጓይ በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ቱርኪዬ ያለ ምንም ነጥብ አራተኛ ደረጃን በመያዝ ሃይቲን ተከትላ ከውድድሩ የተሰናበተች ሁለተኛ ሀገር ሆናለች። በዚሁ ምድብ ትናንት ማምሻውን በተደረገ ጨዋታ አሜሪካ አውስራሊያን 2 ለ 0 በማሸነፍ ጥሎ ማለፍ መግባቷን አረጋግጣለች። ቱርኪዬ ከአሜሪካ፣ ፓራጓይ ከአውስትራሊያ የመጨረሻ የምድብ ጨዋታዎች ናቸው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም