ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ባርሴሎና ለሩብ ፍጻሜ አልፏል
Mar 18, 2026 169
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የጥሎ ማለፍ የመልስ ጨዋታ ባርሴሎና ኒውካስል ዩናይትድን 7 ለ 2 ረምርሟል። ማምሻውን በጆሴ አልቫላዴ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ራፊኒያ እና ሮበርት ሌዋንዶውስኪ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን አስቆጥረዋል። ማርክ በርናል እና ፌርሚን ሎፔዝ በጨዋታ ላሚን ያማል በፍጹም ቅጣት ምት ቀሪዎቹን ጎሎች ለባርሴሎና ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አንቶኒ ኢላንጋ ለኒውካስል ግቦቹን አስቆጥሯል። በመጀመሪያ አጋማሽ ተመጣጣኝ ፉክክር በተደረገበት ጨዋታ ባርሴሎና በሁለተኛው አጋማሽ ፍጹም የበላይነት ወስዷል። ባርሴሎና በሁለተኛው 45 አምስት ጎሎችን አስቆጥሯል። የስፔኑ ባርሴሎና በድምር ውጤት 8 ለ 3 በማሸነፍ ለሩብ ፍጻሜ አልፏል። የአምስት ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቡድኑ ስምንት ውስጥ ሲገባ የአሁኑ ለ21ኛ ጊዜ ነው። በሩብ ፍጻሜው ከአትሌቲኮ ማድሪድ እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ አሸናፊ ጋር ይገናኛል። ኒውካስትል ዩናይትድ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት ህልሙ ሳይሳካ ቀርቷል። በተመሳሳይ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ ሊቨርፑል ከጋላታሳራይ፣ ባየር ሙኒክ ከአትላንታ እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከአትሌቲኮ ማድሪድ የጥሎ ማለፍ የመልስ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በሻምፒዮንስ ሊጉ ሩብ ፍጻሜ የሚገቡ ቀሪ አራት ክለቦች የሚለዩባቸው ጨዋታዎች ይደረጋሉ
Mar 18, 2026 136
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የጥሎ ማለፍ መርሐ- ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። ባርሴሎና ከኒውካስትል ዩናይትድ ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ላይ በካምፕ ኑ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሁለቱ ቡድኖች ከሳምንት በፊት በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ባደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ በሚጠበቀው በዚህ ጨዋታ የሚያሸንፈው ቡድን ሩብ ፍጻሜውን ይቀላቀላል። ሊቨርፑል ከጋላታሳራይ ምሽት አምስት ላይ በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቡድኖች ከሳምንት በፊት በራምስ ፓርክ ስታዲየም ተገናኝተው ጋላታሳራይ 1 ለ 0 አሸንፏል። ሊቨርፑል ወደ ሩብ ፍጻሜ ለመግባት ከአንድ ጎል በላይ ልዩነት ማሸነፍ ይጠበቅበታል። ጋላታሳራይ ማሸነፍ ወይም አቻ መውጣት ስምንት ውስጥ እንዲገባ ያደርገዋል። ባየርሙኒክ አተላንታን ምሽት አምስት ላይ በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም ያስተናግዳል። የጀርመኑ ቡድን በመጀመሪያው ጨዋታ 6 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሉ ከፍተኛ ነው። አተላንታ በሂሳባዊ ስሌት ሩብ ፍጻሜ የመቀላቀል እድሉ እጅጉን የጠበበ ነው። ምሽት አምስት ላይ ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከአትሌቲኮ ማድሪድ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አትሌቲኮ ማድሪድ በመጀመሪያው ጨዋታ 5 ለ 2 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። የስፔኑ ክለብ ሩብ ፍጻሜ ለመግባት ቅርብ ነው። በአንጻሩ በውጤት ማጣት ቀውስ የሚገኘው ቶተንሃም ውጤቱን የመቀልበስ ከፍተኛ ዳገት ይጠብቀዋል። ትናንት በተደረጉ የጥሎ ማለፍ የመልስ ጨዋታዎች ሪያል ማድሪድ፣ ፒኤስጂ፣ አርሰናል እና ስፖርቲንግ ሊዝበን ተጋጣሚዎቻቸውን በደርሶ መልስ ውጤት በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜ ገብተዋል።
ሴኔጋል ያሸነፈችው የአፍሪካ ዋንጫ ተነጥቆ ለሞሮኮ ተሰጠ
Mar 18, 2026 199
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ እግር ኳስ ፌዴሬሽን (ካፍ) የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የፍጻሜ ውጤት ተሽሮ ዋንጫው ለሞሮኮ እንዲሰጥ መወሰኑን አስታወቀ። ውሳኔው ከፍተኛ የመነጋገሪያ አጀንዳ ሆኗል። አህጉራዊው የእግር ኳስ የበላይ አካል ከውሳኔው ላይ የደረሰው የፍጻሜውን ጨዋታ ውጤት ላይ ምርመራ ካደረገ በኋላ መሆኑን የካፍ የይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት አስታውቋል። ሞሮኮ ባስተናገደችው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በፍጻሜው ጨዋታ 1 ለ 0 ተሸንፋ ሴኔጋል ዋንጫውን ማንሳቷ የሚታወስ ነው። በፍጻሜው ጨዋታ ለሞሮኮ የተሰጠውን የፍጹም ቅጣት ምት በመቃወም የሴኔጋል ተጫዋቾች ለ15 ደቂቃ ያህል ሜዳ ጥለው መውጣታቸው የውድድሩን ህግ አንቀጽ 84 (Article 84) የሚጥስ ሆኖ መገኘቱን ካፍ ገልጿል። የሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን (FRMF) ያቀረበውን ይግባኝ ለመመርመር የተሰበሰበው የካፍ የይግባኝ ሰሚ ቦርድ የዲሲፕሊን ኮሚቴው ቀደም ብሎ ያስተላለፈውን ውሳኔ በመሻር ዋንጫውን ከሴኔጋል ተነጥቆ ለሞሮኮ እንዲሰጥ ወስኗል። በዚሁ መሰረት ቦርዱ የ1 ለ 0 ውጤቱን በመሻር ሞሮኮ የ3 ለ 0 የፎርፌ ውጤት እንድታገኝ መደረጉን አመልክቷል። ይህ ውሳኔ ሞሮኮ ከ50 ዓመታት በኋላ የአፍሪካ ዋንጫን ለሁለተኛ ጊዜ እንድታነሳ አስችሏታል። ሴኔጋል ለሁለተኛ ጊዜ ያነሳችው የአፍሪካ ዋንጫ ተነጥቃለች። ካፍ ያስተላለፈው ውሳኔ አስገራሚ፣ ታሪካዊ፣ ያልተጠበቀ እና አወዛጋቢ በሚል በእግር ኳስ አፍቃሪን ዘንድ ከፍተኛ መነጋገሪያ ሆኗል። የሴኔጋል እግር ኳስ ፌዴሬሽን በበኩሉ ባወጣው መግለጫ፤ ካፍ ያሳለፈውን ውሳኔ ኢ-ፍትሐዊ እና ተቀባይነት የሌለው ሲል ገልጾታል። ውሳኔው የአፍሪካን እግር ኳስ ገጽታ ያበላሸ ነውም ብሏል። ፌዴሬሽኑ ውሳኔው እንዲታይ ወደ ዓለም አቀፍ የስፖርት ገላጋይ ፍርድ ቤት (CAS) እንደሚወስድ አመልክቷል።
ሪያል ማድሪድ ፒኤስጂ እና አርሰናል ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቀሉ
Mar 17, 2026 198
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የጥሎ ማለፍ የመልስ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሪያል ማድሪድ ማንችስተር ሲቲን 2 ለ 1 አሸንፏል። ቪኒሺስ ጁኒየር በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ለማድሪድ ግቦቹን አስቆጥሯል። አርሊንግ ሃላንድ ለሲቲ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የማንችስተር ሲቲ አምበል በርናንዶ ሲልቫ በ20ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። የ15 ጊዜ የዋንጫው ባለቤት ሪያል ማድሪድ በድምር ውጤት 5 ለ 1 በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። በሌላኛው መርሐ ግብር ፒኤስጂ ቼልሲን 3 ለ 0 አሸንፏል። በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ክቪቻ ክቫራስኬሊያ፣ ብራድሊ ባርኮላ እና ሴኒ ማዩሉ የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ የምዕራብ ለንደኑን ክለብ በድምር ውጤት 8 ለ 2 በመርታት ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሰናል ባየር ሌቨርኩሰንን 2 ለ 0 አሸንፏል። ኤበሬቺ ኤዘ እና ዴክላን ራይስ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ አርሰናል በድምር ውጤት 3 ለ 1 በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜ ገብቷል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ ስፖርቲንግ ሊዝበን ቦዶ ግሊምትን 5 ለ 0 በማሸነፍ በድምር ውጤት 5 ለ 3 በመርታት ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል።
ስፖርቲንግ ሊዝበን የ3 ለ 0 ውጤት በመቀልበስ ለሩብ ፍጻሜ አለፈ
Mar 17, 2026 164
አዲስን አበባ፤ መጋቢት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ስፖርቲንግ ሊዝበን ቦዶ ግሊምትን 5 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በጆሴ አልቫላዴ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ጎንካሎ ኢናሲዮ እና ፖቴ በጨዋታ ሉዊስ ሱዋሬዝ በፍጹም ቅጣት ምት ሶስት ግቦችን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ቡድኖቹ በድምር ውጤት ሶስት አቻ በመሆናቸው ጨዋታው ወደ ጭማሪ ሰዓት አምርቷል። በጭማሪ ሰዓት ማክሲ አራውጆ በ92ኛው እና ራፋኤል ኔል በ121ኛው ደቂቃ ያስቆጠሯቸው ግቦች ስፖርቲንግን አሸናፊ አድርጓል። የፖርቹጋሉ ክለብ የመጀመሪያ ዙር የ3 ለ 0 ውጤት ባልተጠበቀ ሁኔታ ቀልብሶ በድምር ውጤት 5 ለ 3 በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜ የገባ የመጀመሪያ ክለብ ሆኗል። ስፖርቲንግ ሊዝበን ሩብ ፍጻሜ ሲገባ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። በሩብ ፍጻሜው ከአርሰናል እና ባየር ሌቨርኩሰን አሸናፊ ጋር ይጫወታል። ቦዶ ግሊምት ሩብ ፍጻሜ ለመጀመሪያ ጊዜ የመግባት ህልሙ አልተሳካም። የቦዶ ግሊምት የሻምፒዮንስ ሊግ መልካም ግስጋሴ ጥሎ ማለፍ ላይ ተገቷል። በአሁኑ ሰዓት ሪያል ማድሪድ ከማንችስተር ሲቲ፣ ቼልሲ ከፒኤስጂ እና አርሰናል ከባየር ሌቨርኩሰን ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል። ጨዋታዎቹ ወደ ሩብ ፍጻሜ የሚያልፉ ክለቦች የሚለዩባቸው ናቸው።
መቻል በድል ጉዞው ቀጥሏል
Mar 17, 2026 93
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ19ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር መቻል ይርጋጨፌ ቡናን 4 ለ 1 ረቷል። በአበበ በቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሴናፍ ዋቁማ፣ መዲና አወል፣ ቱሪስት ለማ እና ትንቢተ ሳሙኤል የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ቤተልሄም ፈርኦን ለይርጋጨፌ ቡና ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የመቻሏ ጽዮን ፈየራ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው መቻል በ41 ነጥብ ደረጃውን ከአራተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ያሸነፋቸውን ጨዋታዎች ብዛት 12 አድርሷል። በአንጻሩ በሊጉ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ይርጋጨፌ ቡና በ11 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት 11 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ በተደረገ ሌላኛው ጨዋታ ሲዳማ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 19ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የ20ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከመጋቢት 11 እስከ 13 2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
ሲዳማ ቡና ተከታታይ ድሉን አስመዘገበ
Mar 17, 2026 89
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት ሲዳማ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ በቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ምትኬ ብርሃኑ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥራለች። ብሩክታዊት አየለ ለአዲስ አበባ ከተማ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ሁለት ግቦችን ያስቆጠረችው የሲዳማ ቡናዋ ምትኬ ብርሃኑ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በ27 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። በአጠቃላይ በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ድሉን አሳክቷል። በአንጻሩ በሊጉ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዲስ አበባ ከተማ በስምንት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃ ይዟል። አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ በርካታ ሽንፈቶችን ያስተናገደ ቡድን ነው። በውድድር ዓመቱ ያሸነፋቸው ጨዋታዎች ብዛት ሁለት ብቻ ናቸው።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
Mar 17, 2026 99
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ አዲስ አበባ ከተማ ከሲዳማ ቡና በአበበ በቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አበባ ከተማ በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 18 ጨዋታዎች መካከል ያሸነፈው ሁለት ጊዜ ብቻ ነው። በ14ቱ ሲሸነፍ በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር 39 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በስምንት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ካደረጋቸው 18 ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ያሸነፈው ሲዳማ ቡና በበኩሉ ስምንት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 17 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 23 ግቦች ተቆጥረውበታል። ሲዳማ ቡና በ24 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አዲስ አበባ ከተማ ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ሲዳማ ቡና በ18ኛ ሳምንት ሲዳማ ቡና ባህር ዳር ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በተያያዘም ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ይርጋጨፌ ቡና ከመቻል በአበበ በቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ 18 ጨዋታዎችን በማድረግ ሁለት ሲያሸንፍ በ11ዱ ተሸንፏል። አምስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ስምንት ግቦችን ሲያስቆጥር 26 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በ11 ነጥብ 11 ደረጃን ይዟል። መቻል በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው 18 ጨዋታዎች በ11ዱ ድል ሲቀናው ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በአምስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። 32 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 10 ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ38 ነጥብ አራተኛ ላይ ተቀምጧል። ይርጋጨፌ ቡና ባለፉት 10 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። መቻል ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ድል ቀንቶታል። ጨዋታው ይርጋጨፌ ቡና ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ መቻል በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው።
በሻምፒዮንስ ሊግ ማንችስተር ሲቲ ከሪያል ማድሪድ ቼልሲ ከፒኤስጂ የሚያደርጓቸው ተጠባቂ የመልስ ጨዋታዎች
Mar 17, 2026 138
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አራት የጥሎ ማለፍ የመልስ ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ምሽት አምስት ላይ ማንችስተር ሲቲ ከሪያል ማድሪድ በኢትሃድ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሁለቱ ቡድኖች ከሳምንት በፊት በበርናባው ስታዲየም ባደረጉት ጨዋታ ሪያል ማድሪድ 3 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ሪያል ማድሪድ ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሉ ሰፊ ነው። ማንችስተር ሲቲ ወደ ቀጣዩ ዙር ለማለፍ ከሶስት ጎል በላይ ልዩነት ማሸነፍ ይጠበቅበታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ቼልሲ ከፒኤስጂ ምሽት አምስት ላይ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቡድኖች በፓርክ ደ ፕሪንስ ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ፒኤስጂ 5 ለ 2 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ባለሜዳው ቼልሲ ውጤቱን የመቀልበስ ከባድ ፈተና ይጠብቀዋል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሉ የሰፋ ነው። አርሰናል ከባየር ሌቨርኩሰን ምሽት አምስት ላይ በኤምሬትስ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቡድኖቹ በመጀመሪያ ጨዋታ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው አርሰናል በዘንድሮ የውድድር ዓመት አቻ የወጣበት መርሐ ግብር ነው። በጨዋታው የሚያሸንፈው ቡድን ለሩብ ፍጻሜ ያልፋል። ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ላይ ስፖርቲንግ ሊዝበን ከቦዶ ግሊምት በጆሴ አልቫላዴ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በመጀመሪያው ጨዋታ ቦዶ ግሊምት 3 ለ 0 አሸንፏል። የኖርዌው ቡድን ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሉ ሰፊ ነው።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዝግጅቱን ጀመረ
Mar 16, 2026 254
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ለሚያደርገው የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ዝግጅቱን ዛሬ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሜዳ ማድረግ ጀምሯል። ቡድኑ የመጀመርያ ልምምድ ላይ ጥሪ ከተደረገላቸው ተጫዋቾች መካከል ከሀገር ውጪ ክለቦች ከሚገኙት ጋቶች ፓኖም እና ከነዓን ማርክነህ በቀር ሁሉም ተጫዋቾች መገኘታቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የብሔራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ለማጣሪያ ጨዋታው ለ23 ተጫዋቾች ጥሪ ማድረጋቸው የሚታወስ ነው። ኢትዮጵያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር የማጣሪያ ጨዋታዎቿን መጋቢት 18 እና 22 ቀን 2018 ዓ.ም ታደርጋለች። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በኬንያ፣ ታንዛንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት እ.አ.አ ጁን 2027 ይካሄዳል።
ድሬዳዋ ከተማ እና ሸገር ከተማ ነጥብ ተጋሩ
Mar 16, 2026 138
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ19ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ድሬዳዋ ከተማ እና ሸገር ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማርታ ወልዴ በሰባተኛው ደቂቃ ባስቆጠረችው ግብ ሸገር ከተማ መሪ ሆኗል። ከእረፍት መልስ ህይወት አመንቴ በ54ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈችው ጎል ለድሬዳዋ ከተማ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። የድሬዳዋ ከተማዋ መአዛ አብደላ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ ድሬዳዋ ከተማ በ20 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሸገር ከተማ በ38 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቡድኑ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ማስመዝገብ አልቻለም። ዛሬ በተደረጉ የ19ኛ ሳምንት ሌሎች ጨዋታዎች ባህር ዳር ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 ሲያሸንፍ ሃዋሳ ከተማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ባህር ዳር ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 16, 2026 97
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ19ኛ ሳምንት ጨዋታ ባህር ዳር ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው መርሐ-ግብር ዓይናለም መኮንን በ45ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። የባህር ዳር ከተማዋ መንደሪን ታደሰ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከአምስት ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ባህር ዳር ከተማ በ13 ነጥብ ደረጃውን ከ12ኛ ወደ 11ኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ አራተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ በ10 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። አርባምንጭ የዛሬውን ጨምሮ ባለፉት 12 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።
በተጠባቂው ጨዋታ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሃዋሳ ከተማ ጋር አቻ ተለያየ
Mar 16, 2026 100
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ሃዋሳ ከተማ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታው ረፋድ ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተካሄዷል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። የሃዋሳ ከተማዋ ታሪኳ ጴጥሮስ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ50 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። የሊጉን መሪነት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዳግም የመረከብ እድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተመሳሳይ 50 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ ሊጉን መምራት ጀምሯል። ሃዋሳ ከተማ በ39 ነጥብ ደረጃውን ከአራተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሃዋሳ ከተማ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Mar 16, 2026 119
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሃዋሳ ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ይጫወታሉ። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 18 ጨዋታዎች 11ዱን ሲያሸንፍ ሽንፈት ያስተናገደው ሁለት ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 33 ግቦችን ሲያስቆጥር 12 ግቦችን አስተናግዷል። ሃዋሳ በ38 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው 18 ጨዋታዎች መካከል በ16ቱ ድል ሲቀናው የተሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ወጥቷል። 43 ጎሎችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ በተመሳሳይ 10 ግቦች ተቆጥረውበታል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ49 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሃዋሳ ከተማ ካሸነፈ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሶስት ነጥብ የሊጉን መሪነት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዳግም መረከብ ያስችለዋል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። ድሬዳዋ ከተማ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሊጉ ስድስት ጨዋታዎችን በድል የተወጣው ድሬዳዋ ከተማ 11 ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አንድ ጨዋታ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 16 ግቦቹን ሲያስቆጥር 29 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ድሬዳዋ ከተማ በ19 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ሸገር ከተማ በውድድር ዓመቱ ባካሄዳቸው 18 ጨዋታዎች 15ቱን አሸንፎ በአምስቱ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይቷል። 31 ግቦችን ሲያስቆጥር 18 ጎሎች ገብተውበታል። ቡድኑ በ37 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ ከሶስት ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ ካሸነፈ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ጋር ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በተመሳሳይ 10 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ ካሸነፈ 11 ጨዋታዎች አልፈዋል። ባህር ዳር ከተማ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ።
ሊቨርፑል እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ አቻ ተለያዩ
Mar 15, 2026 238
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት ሊቨርፑል እና ቶተንሃም ሆትስፐርስን ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። ማምሻውን በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ዶምኒክ ስቦዝላይ በ18ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ በቅጣት ምት ያስቆጠረው ግብ ቀያዮቹን መሪ አድርጓል። ሪቻርልሰን በ90ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል ቶተንሃም አንድ ነጥብ አግኝቷል። በጨዋታው ሊቨርፑል የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ቶተንሃም ግልጽ የግብ እድሎችን በመፍጠር ተሽሎ ተገኝቷል። ሊቨርፑል በ49 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አምሰተኛ ከፍ አድርጓል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ለማግኘት በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥሏል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ30 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። የመውረድ አደጋ ውስጥ ያለበት ቶተንሃም ባለፉት 12 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ30ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ አስቶንቪላን 3 ለ 1 አሸንፏል። ክሪስታል ፓላስ ከሊድስ ዩናይትድ፣ ኖቲንግሃም ፎረስት ከፉልሃም ያደረጉት ጨዋታ በተመሳሳይ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የ30ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ነገ ብሬንትፎርድ ከዎልቭስ ጋር በሚያደርጉት ጨዋታ ይጠናቀቃል።
ማንችስተር ዩናይትድ አስቶንቪላን በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል
Mar 15, 2026 195
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ማንችስተር ዩናይትድ አስቶንቪላ 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ካሲሚሮ፣ ማትያስ ኩንሃ እና ቤንጃሚን ሼስኮ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሮስ ባርክሌይ ለአስቶንቪላ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ዩናይትድ በ54 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ዩናይትድ በሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አስቶንቪላ በ51 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቪላ ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። የማንችስተር ዩናይትዱ ብሩኖ ፈርናንዴዝ ዘንድሮ በሊጉ ለግብ አመቻችቶ ያቀበላቸውን ኳሶች ብዛት 16 አድርሷል። በዛሬው ጨዋታም በሁለት ግቦች ላይ ተሳትፎ ነበረው። ይህም ዴቪድ ቤካም በዩናይትድ በአንድ የውድድር ዓመት 15 ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን የማቀበል ክብረ ወሰን እንዲሰብር አድርጎታል። በተመሳሳይ ሰዓት በተደረጉ የ30ኛ ጨዋታዎች ክሪስታል ፓላስ ከሊድስ ዩናይትድ፣ ኖቲንግሃም ፎረስት ከፉልሃም በተመሳሳይ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ በድል ጉዞው ጥሏል
Mar 15, 2026 162
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ24ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ነገሌ አርሲን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሀሰን ሁሴን ግቦቹን አስቆጥሯል። ካሜሮናዊው የነገሌ አርሲ ተጫዋች ፓስካል ኢቡሲ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በሊጉ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ37 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ነገሌ አርሲ በ38 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሁለተኛ ደረጃን ከሃዋሳ ከተማ የመረከብ እድሉን አልተጠቀመበትም። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ-ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ወላይታ ድቻ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። መቀሌ 70 እንደርታ በ23 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። ወላይታ ድቻ በ27 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 24ኛ ሳምንት ተጠናቋል። ፕሪሚየር ሊጉ ኢትዮጵያ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ በምታደርጋቸው የማጣሪያ ጨዋታዎች ምክንያት ይቋረጣል። ውድድሩ መጋቢት 25 ቀን 2018 ዓ.ም በ25ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር እንደሚመለስ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
አትሌት ፎቴን ተስፋይ ለመጀመሪያ ጊዜ ባደረገችው የማራቶን ውድድር አሸነፈች
Mar 15, 2026 111
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በባርሴሎና ማራቶን በሴቶች ውድድር አትሌት ፎቴን ተስፋይ አሸንፋለች። አትሌት ፎቴን ውድድሩን ለማጠናቀቅ 2 ሰዓት ከ10 ደቂቃ ከ53 ሰከንድ ፈጅቶባታል። በዚህም መሠረት የቦታውን ክብረወሰን በመስበር ያሸነፈች ሲሆን፤ በርቀቱ የዓለም ሁለተኛው ፈጣን ሰዓትም አስመዝግባለች። አትሌቷ በመጀመሪያ የማራቶን ውድድሯ ድል ቀንቷታል። በውድድሩ የተሳተፉት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ዘይነባ ይመር ሶስተኛ፣ ጫልቱ ጭምዴሳ አራተኛ እና ያልጋነሽ እስከመች አምስተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድራቸውን አጠናቅቀዋል ። የባርሴሎና ማራቶን በዓለም አትሌቲክስ የነሐስ ደረጃ የተሰጠው የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር ነው።
ቦሌ ክፍለ ከተማ እና አዳማ ከተማ ነጥብ ተጋሩ
Mar 15, 2026 96
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ቦሌ ክፍለ ከተማ እና አዳማ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ፍቅረአዲስ ገዛኸኝ በ34ኛው ደቂቃ ያስቆጠረችው ጎል ቦሌ ክፍለ ከተማን መሪ አድርጓል። ሔለን መሰለ በ62ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈችው ጎል ለአዳማ ከተማ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። የአዳማ ከተማዋ ነጻነት መና የጨዋታው ኮከብ ሆና መርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ ቦሌ ክፍለ ከተማ በ31 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ዛሬ አስቀድሞ በተካሄደ የ19ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ልደታ ክፍለ ከተማን 5 ለ 0 አሸንፏል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሊጉ መሪ ሆነ
Mar 15, 2026 98
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ልደታ ክፍለ ከተማን 5 ለ 0 ረትቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ፤ እሙሽ ዳንኤል ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር እፀገነት ግርማ፣ ንግሥት በቀለ እና ታሪኳ ደቤሶ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሁለት ግቦችን ያስቆጠረችው እሙሽ ዳንኤል የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ 16ኛ ድሉን ያስመዘገበው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ50 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በጊዜያዊነት ተረክቧል። በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ልደታ ክፍለ ከተማ በ15 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል።