ቀጥታ፡
ስፖርት
ኢትዮጵያን የአፍሪካና የዓለም የስፖርት ማዕከል የሚያደርጉ መሰረተ ልማቶች ግንባታ ተጠናክሮ ቀጥሏል
Jun 29, 2026 170
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 22/2018 (ኢዜአ):-ኢትዮጵያን የአፍሪካና የአለም የስፖርት ማዕከል ለማድረግ የሚያስችሉ የዲፕሎማሲና የስፖርት መሰረተ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር መኪዩ መሐመድ ለኢዜአ እንዳሉት ከለውጡ ወዲህ ለስፖርት ልማት ዘርፍ የተሰጠው ትኩረት ዘርፈ ብዙ ለውጥ ማስመዝገብ አስችሏል። በዓለም አቀፍ መድረኮች የኢትዮጵያን ውክልና በማሳደግ የሀገሪቱን ገጽታ ለመገንባትና የስፖርት ዲፕሎማሲን ለማጠናከር እየተሰራ ነው ብለዋል። በዚህም 14 የሀገር አቀፍ ስፖርት ማህበራት አመራሮች በአህጉር እና በዓለም አቀፍ ደረጃ አመራር በመሆን እያገለገሉ መሆናቸውንና ይህ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። ኢትዮጵያውያን በዓለም አቀፍ የስፖርት ውድድር መድረክ ያላቸው ተሳትፎና ውጤታማነት እያደገ መሆኑንም አስረድተዋል። ኢትዮጵያ አህጉር አቀፍና ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ሁነቶችን እያስተናገደች መሆኗን ጠቅሰው፣ ይህም የሀገሪቱን ገፅታ ለመገንባት ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልፀዋል። አዲስ አበባን የአፍሪካና የዓለም ስፖርታዊ ሁነቶች ማዕከል በማድረግ ኢትዮጵያን ከዘርፉ የበለጠ ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት መሰረተ ልማት የማስፋፊያ ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን አንስተው፣ አምስት ትላልቅ ስታዲየሞች የዓለም አቀፍ ስታንዳርዶችን እንዲያሟሉ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡    
ኔዘርላንድስ ከሞሮኮ ፤ ተጠባቂው የጥሎ ማለፍ ፍልሚያ
Jun 29, 2026 249
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ዛሬ ሶስት የ32 ኛ ዙር የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ ኔዘርላንድስ ከሞሮኮ በሞንቴሬይ ስታዲየም የሚያከናውኑት ጨዋታ የእግር ኳስ አፍቃሪያንን ትኩረት ስቧል። ኔዘርላንድስ በምድብ ስድስት በሰባት ነጥብ መሪነት አጠናቃለች። በምድብ ሶስት የነበረችው ሞሮኮ በሰባት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። የሰሜን ምዕራብ አውሮፓዋ ሀገር ወደ ጥሎ ማለፍ ስትገባ የአሁኑ ለ12ኛ ጊዜ ነው። ለሶስተኛ ጊዜ ወደ ጥሎ ማለፍ የገባችው ሞሮኮ በ22ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ የደረሰች የመጀመሪያ አፍሪካዊ ሀገር በመሆን ታሪክ ሰርታለች። ሁለቱ ሀገራት እ.አ.አ 1994 አሜሪካ ባዘጋጀችው 15ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በምድብ ምዕራፍ ተገናኝተው ኔዘርላንድስ 2 ለ 1 ማሸነፏ የሚታወስ ነው። ሀገራቱ ከ32 ዓመታት በኋላ በዓለም መድረክ በድጋሚ ተገናኝተዋል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ሞሮኮ ተገማችነቷን አስጠብቃ ለመቀጠል ጠንካራዋን ኔዘርላንድ ማሸነፍ ይኖርባታል። በሌላኛው የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ ብራዚል ከጃፓን በሂውስተን ስታዲየም ይጫወታሉ። የአምስት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ብራዚል በምድብ ሶስት በሰባት ነጥብ መሪ ሆና በማጠናቀቅ ወደ ጥሎ ማለፉ ገብታለች። ብራዚል በዓለም ዋንጫዋ ወደ ጥሎ ማለፍ ምዕራፍ ስትሸጋገር የአሁኑ ለ19ኛ ጊዜ ነው። በሁሉም የዓለም ዋንጫዎች የተሳተፈች ብቸኛ ሀገርም ናት። ተጋጣሚዋ ጃፓን በምድብ ስድስት በአምስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ በዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ታሪኳ ለአምስተኛ ጊዜ ወደ ጥሎ ማለፍ መግባት ችላለች። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ያደረጓቸውን ሁለት ጨዋታዎች ብራዚል በማሸነፍ የበላይነቱን ይዛለች። ጃፓን ብራዚልን በውድድር እና በወዳጅነት ጨዋታዎች አሸንፋ አታውቅም። ምሽት 5 ሰዓት ከ30 ጀርመን ከፓራጓይ በቦስተን ስታዲየም ይጫወታሉ። የአራት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ጀርመን በምድብ አምስት በስድስት ነጥብ የምድቡ መሪ ሆና አጠናቃለች። ተጋጣሚዋ ፓራጓይ በምድብ በአራት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ በምርጥ ሶስተኛነት ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። ጀርመን ወደ ጥሎ ማለፍ ስታልፍ በዓለም ዋንጫ ተሳትፎዋ ታሪክ የአሁኑ ለ14ኛ ጊዜ ነው። ተጋጣሚዋ ፓራጓይ ወደ ጥሎ ስትገባ ለአምስተኛ ጊዜ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። ጃፓን እና ኮሪያ ሪፐብሊክ እ.አ.አ በ2002 በጣምራ ባዘጋጁት 17ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በጥሎ ማለፉ ተገናኝተው ጀርመን 1 ለ 0 በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅላች። በወቅቱ እስከ መጨረሻው ተጉዛ ዋንጫውን አንስታለች። ሁለቱ ሀገራት ከ24 ዓመታት በኋላ በድጋሚ በጥሎ ማለፍ ምዕራፍ ላይ ተገናኝተዋል።
ሸገር ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ መቆየቱን አረጋገጠ
Jun 28, 2026 645
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሸገር ከተማ መቻልን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፍቅሩ አለማየሁ እና ያሬድ መኮንን ግቦቹን አስቆጥረዋል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ድሉን ያስመዘገበው ሸገር ከተማ በ47 ነጥብ ከነበረበት 15ኛ ደረጃ ወደ 10ኛ ከፍ ብሏል። ዘንድሮ ከከፍተኛ ሊግ ያደገው ሸገር ከተማ በሊጉ መቆየቱን አረጋግጧል። በሊጉ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው መቻል በ56 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ሃዋሳ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሀሰን ሁሴን በ34ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ኢትዮ ኤሌክትሪክ መሪ ሆኗል። ጌታነህ ከበደ በ61ኛው ደቂቃ የሃዋሳ ከተማን የአቻነት ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ51 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ሃዋሳ ከተማ በ50 ነጥብ ስምንት ደረጃ ላይ ይገኛል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ የ37ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ሻምፒዮኑ ሲዳማ ቡና ባህር ዳር ከተማን 1 ለ 0፣ ወላይታ ድቻ አዳማ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 37ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የፕሪሚየር ሊጉ የመጨረሻ ሳምንት (38ኛ ሳምንት) መርሐ ግብር በቀጣይ ሳምንት ይካሄዳል።
የ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ደቡብ አፍሪካ እና ካናዳ በሚያደርጉት ጨዋታ ይጀመራል
Jun 28, 2026 421
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):- የዓለም አቀፉ እግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) በዓለም ዋንጫ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ተግባራዊ ያደረገው የ32 ዙር (Round of 32) የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል። የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብሩ ደቡብ አፍሪካ እና ካናዳ በሚያደርጉት ጨዋታ ይጀመራል። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በሎስ አንጀለስ ስታዲየም ይካሄዳል። ደቡብ አፍሪካ በምድብ አንድ በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በተለይም በምድብ የመጨረሻ ጨዋታ ኮሪያ ሪፐብሊክን ማሸነፏ ወደ ጥሎ ማለፍ እንድትገባ አስችሏታል። ተጋጣሚዋ ካናዳ በምድብ ሁለት በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ መጨረሷ ይታወቃል። ከዓለም ዋንጫ አስተናጋጅ ሀገራት መካከል አንዷ የሆነችው ካናዳ በምድቧ ኳታርን 6 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት ያሸነፈችበት ጨዋታ በውድድሩ ታሪክ ያስመዘገበችው የመጀመሪያ ድሏ ሆኗል። ደቡብ አፍሪካ እና ካናዳ ወደ ጥሎ ማለፍ ሲገቡ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። በዓለም ዋንጫው እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ። ከዚህ ቀደም የነበራቸው ብቸኛ ግንኙነት እ.አ.አ በ2007 በደርባን ያደረጉት የወዳጅነት ጨዋታ ነው። በወቅቱ ደቡብ አፍሪካ ቴኮ ሞዲሴ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ባስቆጠራቸው ጎሎች 2 ለ 0 ማሸነፏ የሚታወስ ነው። ሁለቱ ሀገራት ከእግር ኳስ ውጪ በዓለም መድረክ በራግቢ እና ክሪኬት ስፖርቶች ተቀናቃኝነት ያላቸው ሀገራት ናቸው። ሀገራቱ ወደ ቀጣዩ የጥሎ ማለፍ ምዕራፍ ለመሸጋገር የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። አሸናፊው ሀገር ወደ 16 ውስጥ መግባቱን ያረጋግጣል። የ32 ዙር (Round of 32) የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር እስከ ሰኔ 26 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በአሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ ጣምራ አዘጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ለመጀመሪያ ጊዜ 48 ሀገራት እየተሳተፉ ይገኛል። የተሳታፊ ሀገራት ቁጥር ወደ 48 በማደጉ ምክንያት የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) የ32 ዙር (Round of 32) የጥሎ ማለፍ ፎርማት በውድድሩ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ተግባራዊ አድርጓል። በምድብ ጨዋታዎች ወቅት 48ቱ አገራት በ12 ምድቦች (ከምድብ 1 እስከ 12) ተከፍለው ጨዋታቸውን አድርገዋል። በ12ቱ ምድቦች አንደኛ እና ሁለተኛ የወጡ 24 ሀገራት እንዲሁም ከየምድባቸው በሶስተኛነት ካጠናቀቁት 12 ብሔራዊ ቡድኖች መካከል ስምንቱ በምርጥ ሶስተኛነት ወደ ጥሎ ማለፍ ዙሩ ገብተዋል።
የሊጉ ሻምፒዮን ሲዳማ ቡና ከባህር ዳር ከተማ ጋር ይጫወታል
Jun 28, 2026 248
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ባህር ዳር ከተማ ከሲዳማ ቡና በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባህር ዳር ከተማ በ47 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ሻምፒዮኑ ሲዳማ ቡና በ65 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ባለፉት አራት ጨዋታዎች ድል ያልቀናው ባህር ዳር ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይፋለማል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በበርካታ ጨዋታዎች (20 ጊዜ) አቻ የተለያየ ቡድን ነው። በ36ኛ ሳምንት ከነገሌ አርሲ ጋር አንድ አቻ በመለያየት በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የሊጉን ዋንጫ ማንሳቱን ያረጋገጠው ሲዳማ ቡና ዓመቱን የተሻለ ነጥብ ሰብስቦ ለማጠናቀቅ የዛሬውን ጨዋታ ማሸነፍ ይጠበቅበታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ሸገር ከተማ ከመቻል ከቀኑ 10 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሸገር ከተማ በ44 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። መቻል በ56 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሸገር ከተማ ካሸነፈ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል። በ36ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ መድንን 1 ለ 0 የረታው መቻል ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ከቀኑ 10 ሰዓት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሃዋሳ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ50 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ሃዋሳ ከተማ በ49 ነጥብ 19ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ36ኛ ሳምንት ወላይታ ድቻን 2 ለ 1 በመርታት ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ማግኘት ያልቻለው ሃዋሳ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይፋለማል። በተያያዘም ትናንት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት አዳማ ከተማ እና ወላይታ ድቻ ሊያደርጉት የነበረው ጨዋታ በከፍተኛ ዝናብ ምክንያት ሳይካሄድ ቀርቷል። የሊጉ አክሲዮን ማህበር ባስተላለፈው ውሳኔ መሰረት ጨዋታው ዛሬ ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይከናወናል። አዳማ ከተማ በ43 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዛል። ወላይታ ድቻ በ47 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ36ኛ ሳምንት ከመቀሌ 70 እንደርታ ጋር ያለ ግብ አቻ የተለያየው አዳማ ከተማ ዛሬ ካሸነፈ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል። በ36ኛ ሳምንት በኢትዮ ኤሌክትሪክ ሽንፈት የ2 ለ 1 ያስተናገደው ወላይታ ድቻ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታል።
ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና አልጄሪያ ጥሎ ማለፉን ተቀላቀሉ
Jun 28, 2026 248
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ 10 እና 11 የመጨረሻ ጨዋታዎች ተደርገዋል። በአትላንታ ስታዲየም በተካሄደው የምድብ 11 ጨዋታ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ኡዝቤኪስታንን 3 ለ 1 አሸንፋለች። ዮአን ዊሳ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ፊስተን ማዬሌ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ኤልዶር ሾሙሮዶቭ የኡዝቤኪስታንን ብቸኛ ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የጨዋታ ብልጫ ነበራት። ሁለት ግቦችን ያስቆረው ዮአን ዊሳ የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በአራት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቅ በምርጥ ሶስተኝነት ጥሎ ማለፏን ለመጀመሪያ ጊዜ ተቀላቅላለች። ሁሉንም የምድብ ጨዋታዎቿን የተሸነፈችው ኡዝቤኪስታን ያለ ምንም ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዛ ከውድድሩ ተሰናብታለች። ሀገሪቷ በዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ተሳትፎዋን ማድረጓ ይታወቃል። በዚሁ ምድብ በሚያሚ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ኮሎምቢያ እና ፖርቹጋል ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ኮሎምቢያ በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ ሆና ስታጠናቀቅ ፖርቹጋል በአምስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ሁለቱ ሀገራት አስቀድመው ጥሎ ማለፍ መግባታቸው ይታወቃል። በተያያዘም የምድብ 10 የመጨረሻ ጨዋታዎች ከእኩለ ሌሊት በኋላ ተከናውነዋል። በካንሳስ ሲቲ በተካሄደው ጨዋታ አልጄሪያ እና ኦስትሪያ ሶስት አቻ ተለያይተዋል። ሪያድ ማህሬዝ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ራፊክ ቤልግሃሊ ቀሪዋን ጎል ለአልጄሪያ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ማርኮ አርናውቶቪች፣ ማርሴል ሳቢትዘር እና ሳሳ ካላድዚች የኦስትሪያን ግቦች አስቆጥረዋል። በጨዋታው አልጄሪያ የተሻለ እንቅስቃሴ አድርጋለች የአልጄሪያው አምበል ሪያድ ማህሬዝ የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ አልጄሪያ በአራት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ በምርጥ ሶስተኝነት ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። ይህንን ተከትሎም በዓለም ዋንጫ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ 10 ሀገራት ያሳተፈችው አፍሪካ ከቱኒዚያ በስተቀር ዘጠኙ ሀገራት ወደ ጥሎ ማለፉ ገብተዋል። ይህም ለአፍሪካ መልካም ስኬት የሚባል ነው። ኦስትሪያም በተመሳሳይ አራት ነጥብ በግብ ክፍያ በልጣ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ወደ ጥሎ ማለፉ ገብታለች። በዚሁ ምድብ ሌላኛው መርሐ ግብር አርጀንቲና ጆርዳንን 3 ለ 1 አሸንፋለች። ሊዮኔል ሜሲ፣ ላውታሮ ማርቲኔዝ ( ፍጹም ቅጣት ምት) እና ጂኦቫኒ ሎ ሴልሶ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሙሳ ታማሪ የጆርዳንን ብቸኛ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የ39 ዓመቱ ሊዮኔል ሜሲ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ ስድስት በማድረስ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን አጠናክሯል። በአጠቃላይ በዓለም ዋንጫው ከመረብ ላይ ያሳረፋቸውን ግቦች ብዛት ወደ 19 በማሳደግ የውድድሩን የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት ማጠናከር ችሏል። ለአርጀንቲናም 123ኛ ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የዓለም ዋንጫ ባለቤት አርጀንቲና በዘጠኝ ነጥብ የምድቡ መሪ ሆና አጠናቃለች። ቡድኑ ቀድሞ ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቱ ይታወቃል። ጆርዳን ያለ ምንም ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዛ ከውድድሩ ተሰናብታለች። ጆርዳን በዓለም ዋንጫው ለመጀመሪያ ጊዜ መሳተፏ ይታወቃል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የምድብ መርሐ ግብር ተጠናቋል። የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል።
በወራጅ ቀጠና የሚገኘው ምድረ ገነት ሽሬ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Jun 27, 2026 356
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ምድረ ገነት ሽሬ ኢትዮጵያ መድንን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አዲስ ተስፋዬ፣ ዳንኤል ዳርጌ እና አቤል ማሙሽ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ምድረ ገነት ሽሬ በ42 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን ያስመዘገበው ምድረ ገነት ሽሬ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት እያደረገ ባለው ትግል ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ቡድኑ በሊጉ የመቆየት ተስፋውን ለመለምለም በመጨረሻው ሳምንት ሸገር ከተማን ማሸነፍ ይጠበቅበታል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ መድን በ46 ነጥብ ከነበረበት 12ኛ ደረጃ ወደ 13ኛ ዝቅ ብሏል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረገ የ37ኛ ሳምንት ጨዋታ ሀድያ ሆሳዕና እና ድሬዳዋ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ውጤቱን ተከትሎ ድሬዳዋ ከተማ ከሊጉ መውረዱ ተረጋግጧል። በተያያዘም ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት አዳማ ከተማ እና ወላይታ ድቻ ሊያደርጉት የነበረው ጨዋታ በከፍተኛ ዝናብ ምክንያት ሳይካሄድ የቀረ ሲሆን ጨዋታው ነገ ከረፋዱ አራት ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም እንደሚከናወን የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
ድሬዳዋ ከተማ ከሊጉ የወረደ ሶስተኛ ቡድን ሆኗል
Jun 27, 2026 295
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሀዲያ ሆሳዕና እና ድሬዳዋ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብሩክ በየነ በ44ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ሀዲያ ሆሳዕና መሪ ሆኗል። አቤል ነጋሽ በ56ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ግብ ድሬዳዋ ከተማን አቻ አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ ድሬዳዋ ከተማ አንድ ጨዋታ እየቀረው በ39 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ወርዷል። ድሬዳዋ ከተማ ከሊጉ የወረደው ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ ነው። አርባምንጭ ከተማ እና መቀሌ 70 እንደርታን ተከትሎ ከሊጉ የወረደ ሶስተኛ ቡድን ሆኗል። ቀሪ የሚወርደው አንድ ክለብ በቀሪ ጨዋታዎች የሚለይ ይሆናል። ነጥብ የተጋራው ሀዲያ ሆሳዕና በ47 ነጥብ ደረጃውን ከ13ኛ ወደ 11ኛ ከፍ አድርጓል። በተያያዘም ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት አዳማ ከተማ እና ወላይታ ድቻ ሊያደርጉት የነበረው ጨዋታ በከፍተኛ ዝናብ ምክንያት ሳይካሄድ ቀርቷል። ጨዋታው ነገ ከረፋዱ አራት ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም እንዲደረግ መወሰኑን የሊጉ የውድድርና ስነስርዓት ኮሚቴ አስታውቋል።
ሴኔጋል ጥሎ ማለፉን ተቀላቀለች
Jun 27, 2026 409
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ ሰባት የመጨረሻ ጨዋታዎች ማለዳ ላይ ተደርገዋል። በቢሲ ፕሌስ ቫንኩቨር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቤልጂየም ኒውዝላንድን 5 ለ 1 ረታለች። ሊያንድሮ ትሮሳርድ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኬቨን ደ ብሮይን፣ ሮሜሎ ሉካኩ እና አሌክሲስ ሳሌማከርስ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሉካኩ በአጠቃላይ በዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ስድስት አድርሷል። ኤሊጃህ ጀስት ለኒውዝላንድ ብቸኛውን ግብ አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትላ ቤልጂየም በአምስት ነጥብ ምድቡን በመሪነት በማጠናቀቅ ወደ ጥሎ ማለፉ ገብታለች። ኒውዝላንድ በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በሲያትል ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ግብጽ እና ኢራን አንድ አቻ ተለያይተዋል። መሐሙድ ሳቡር ለግብጽ፣ ራሚን ሬዛያን ለኢራን ግቦቹን አስቆጥረዋል። አስቀድማ ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቷን ያረጋገጠችው ግብጽ በአምስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ኢራን በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በምርጥ ሶስተኛነት ለማለፍ የቀሪ የምድብ ጨዋታዎችን ውጤቶች ትጠብቃለች። የምድብ ስምንት ውጤቶችን ተከትሎ በምድብ ዘጠኝ በሶስት ነጥብ እና በሁለት የግብ ክፍያ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችው ሴኔጋል በምርጥ ሶስተኝነት ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። ይህን ተከትሎም ወደ ጥሎ ማለፉ የገቡ የአፍሪካ ሀገራት ብዛት ሰባት ደርሷል።
የመውረድ ስጋት ያለባቸው ክለቦች የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Jun 27, 2026 293
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይከናወናሉ። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ መድን ከምድረ ገነት ሽሬ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ መድን በ46 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ምድረ ገነት ሽሬ በበኩሉ በ38 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ36ኛ ሳምንት በመቻል 1 ለ 0 የተሸነፈው ኢትዮጵያ መድን ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። መድን የባለፈው ዓመት የሊጉ አሸናፊ እንደነበር ይታወቃል። ባለፉት አራት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ምድረ ገነት ሽሬ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት የዛሬውን ጨዋታ ማሸነፍ ግዴታው ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ሀዲያ ሆሳዕና ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሀዲያ ሆሳዕና በ43 ነጥብ 1ኛ 3ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ድሬዳዋ ከተማ በ38 ነጥብ 18ኛ ደረጃን በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ36ኛ ሳምንት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን 1 ለ 0 ያሸነፈው ሀዲያ ሆሳዕና ካሸነፈ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል። በተመሳሳይ በ36ኛ ሳምንት ሸገር ከተማን 2 ለ 0 ያሸነፈው ድሬዳዋ ከተማ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት ከጨዋታው ሶስት ነጥብ ማግኘት ይጠበቅበታል። ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት አዳማ ከተማ ከወላይታ ድቻ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። አዳማ ከተማ በ43 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዛል። ወላይታ ድቻ በ47 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ36ኛ ሳምንት ከመቀሌ 70 እንደርታ ጋር ያለ ግብ አቻ የተለያየው አዳማ ከተማ ዛሬ ካሸነፈ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል። በተመሳሳይ በ36ኛ ሳምንት በኢትዮ ኤሌክትሪክ የ2 ለ 1 ሽንፈት ያስተናገደው ወላይታ ድቻ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይፋለማል። የዛሬ ጨዋታዎች ላለመውረድ በሚደረገው ትግል ትልቅ ትርጉም የሚሰጣቸው ናቸው።
ከአልጄሪያ እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ማን ወደ ጥሎ ማለፍ ያልፋል?
Jun 27, 2026 196
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ የ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የምድብ መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። በምድብ 12 ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ላይ ክሮሺያ ከጋና በፊላደልፊያ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ክሮሺያ በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ፣ ጋና በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። የደቡብ ምስራቅ አውሮፓዊቷ ሀገር ክሮሺያ ማሸነፍ ቀጥታ ወደ ጥሎ ማለፍ ያስገባታል። የአቻ ውጤት በምርጥ ሶስተኝነት ሊያሳልፋት የሚችልበት እድል አለ። ጋና ትናንት የተደረጉ የምድብ ጨዋታዎችን ተከትሎ ጥሎ ማለፍ መግባቷን አረጋግጣለች። በዚሁ ምድብ ፓናማ ከእንግሊዝ በኒው ዮርክ ኒው ጀርዚ ስታዲየም በተመሳሳይ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ሁለት ጊዜ የተሸነፈችው ፓናማ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በአራት ነጥብ ምድቡን እየመራች የምትገኘው እንግሊዝ የትናንት ውጤቶችን ተከትሎ ወደ ጥሎ ማለፍ ገብታለች። በሌላ በኩል በምድብ 10 የምትገኘው አልጄሪያ ከኦስትሪያ ጋር ከሌሊቱ 11 ሰዓት ላይ በካንሳስ ሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ኦስትሪያ እና አልጄሪያ በተመሳሳይ ሶስት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። የጨዋታው አሸናፊ ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቱን ያረጋግጣል። አቻ መውጣትም ወደ ቀጣዩ ዙር ሊያሳልፋቸው የሚችልበት እድል አለ። የምድቡ መሪ አርጀንቲና ከጆርዳን ከሌሊቱ 11 ሰዓት ላይ በዳላስ ስታዲየም ጋር ትጫወታለች። አርጀንቲና በስድስት ነጥብ ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቷ ይታወቃል። ማሸነፍ ወይም አቻ መውጣት የምድቡ መሪ ሆና እንድታጠናቅቅ ያስችላታል። ለመጀመሪያ ጊዜ በዓለም ዋንጫው ላይ እየተሳተፈች የምትገኘው ጆርዳን ሁለት ጊዜ ተሸንፋ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በተያያዘም የምድብ 11 የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከኡዝቤኪስታን ከሌሊቱ 8 ሰዓት ከ30 በአትላንታ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። የማዕከላዊ አፍሪካዋ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በአንድ ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። ኡዝቤኪስታን ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻው አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ኮንጎ ወደ ጥሎ ማለፍ ለመግባት ያላት ብቸኛ እድል ማሸነፍ ብቻ ነው። በዓለም ዋንጫው ለመጀመሪያ ጊዜ እየተሳተፈች የሚገኘው ኡዝቤኪስታን ማሸነፍ በምርጥ ሶስተኝነት ወደ ጥሎ ማለፉ ሊያስገባት ይችላል። በዚሁ ምድብ ኮሎምቢያ ከፖርቹጋል በተመሳሳይ ከሌሊቱ 8 ሰዓት ከ30 ላይ በሚያሚ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደሰርጋሉ። ኮሎምቢያ በስድስት ነጥብ ከምድቧ ማለፏን አረጋግጣለች። ፖርቹጋል በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፍ መግባቷን አረጋግጣለች። የደቡብ አሜሪካዋ ኮሎምቢያ ካሸነፈች ወይም አቻ ከወጣች የምድቡ መሪ ሆና ታጠናቅቃለች። ፖርቹጋል ማሸነፍ የምድቡ መሪ ሆና እንድታጠናቅቅ ያስችላታል።
ኬፕቨርዴ ለጥሎ ማለፍ አለፈች
Jun 27, 2026 388
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ ዘጠኝ ጨዋታዎች ከእኩለ ሌሊት በኋላ ተደርገዋል። በሂውስተን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኬፕቨርዴ እና ሳዑዲ አረቢያ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ታይቶበታል። የኬፕቨርዴው ዴሮይ ዱአርቴ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ አፍሪካዋቷ ኬፕቨርዴ በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ በመጀመሪያ የዓለም ዋንጫ ተሳትፎዋ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። ኬፕቨርዴ ምንም ሽንፈት እስከ አሁን አላስተናገደችም። ሳዑዲ አረቢያ በሁለት ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በዚሁ ምድብ በጓድላሃራ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ስፔን ኡራጓይን 1 ለ 0 አሸንፋለች። አሌክስ ባኤና በ42ኛው ደቂቃ ግቧን አስቆጥሯል። የኡራጓዩ ኦግስቲን ካኖቢዮ በ94ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ይህም በዓለም ዋንጫው የተመዘዘ 10ኛው ቀይ ካርድ ሆኖ ተመዝግቧል። ስፔን በሰባት ነጥብ የምድብ ስምንት መሪ ሆና በማጠናቀቅ ወደ ጥሎ ማለፉ ገብታለች። ኡራጓይ በሁለት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች። የደቡብ አሜሪካዋ ሀገር ለሁለት ተከታታይ የዓለም ዋንጫዎች ከምድቡ ተሰናብታለች። የምድብ ስምንት ስምንት እና ዘጠኝ ውጤቶችን ተከትሎ ጋና፣ ግብጽ፣ እንግሊዝ፣ ፖርቹጋል እና ፓራጓይ ወደ ጥሎ ማለፉ መግባታቸውን አረጋግጠዋል።
ሴኔጋል ኢራቅን በሰፊ የግብ ልዩነት አሸነፈች
Jun 27, 2026 234
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ ዘጠኝ መርሐ ግብር ሴኔጋል አራቅን 5 ለ 0 ረትታለች። ማምሻውን በቶርንቶ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ተቀይሮ የገባው ፓፕ ጌይ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሀቢብ ዲያራ፣ ኢስማይላ ሳር እና ኢሊማን ንጃይ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አጥቂው ኢስማይላ ሳር በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ሶስት አድርሷል። የኢራቅ ተከላካይ ሬቢን ሱላካ በ13ኛው ደቂቃ በቀይም ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በዓለም ዋንጫው ዘጠነኛው ካርድ ሆኖም ተመዝግቧል። ሴኔጋል በጨዋታው ላይ ከወሰደችው ብልጫ በተጨማሪ ቀይ ካርዱ ፍጹም የበላይነት እንዲኖራት አድርጓል። ሴኔጋል በዓለም ዋንጫ ታሪክ በአንድ ጨዋታ በርካታ ግብ ያስቆጠረች (አምስት) የመጀመሪያ አፍሪካዊ ሀገር ሆናለቾ። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ድሏን ያስመዘገበችው ሴኔጋል በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ሴኔጋል ምርጥ ሶስተኛ ሆና ለማለፍ የሌሎች ምድቦችን ውጤቶች ትጠብቃለች። ዛሬ በሰፊ የግብ ልዩነት ማሸነፏ ተስፋዋ እንዲጨምር አድርጓል። ሁሉንም የምድብ ጨዋታዋን የተሸነፈችው አራቅ ያለ ምንም ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቅ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በዚሁ ምድብ በቦስተን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፈረንሳይ ኖርዌይን 4 ለ 1 አሸንፋለች። ኡስማን ዴምቤሌ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ይህም በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የተቆጠረ ሶስተኛ ሀትሪክ ሆኖ ተመዝግቧል። ዴዚሬ ዱዌ ለፈረንሳይ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቴሎ አስጋርድ የኖርዌይን ብቸኛ ጎል አስቆጥሯል። የኖርዌዩ ጆርገን ስትራንድ ላርሰን በ50ኛው ደቂቃ ፍጹም ቅጣት ምት ስቷል። ውጤቱን ተከትሎ ፈረንሳይ በዘጠኝ ነጥብ የምድቡ መሪ ሆና አጠናቃለች። ፈረንሳይ ከሜክሲኮ በመቀጠል ሁሉንም የምድብ ጨዋታዎቿን ያሸነፈች ሀገር ሆናለች። ኖርዌይ በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። ሁለቱ ሀገራት አስቀድመው ጥሎ ማለፍ መግባታቸው ይታወቃል። በጥሎ ማለፉ ፈረንሳንይ ከስዊድን፣ ኖርዌይ ከኮትዲቯር ይገናኛሉ።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Jun 26, 2026 545
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሰመረ ሀፍታይ በሰባተኛው ደቂቃ ግቧን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከሶሶት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ45 ነጥብ ደረጃውን ከ16ኛ ወደ 14ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ድሉን ያስመዘገበው ወልዋሎ በሊጉ የመቆየት እድሉን ይበልጥ አስፍቷል። በአንጻሩ በሊጉ 16ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ35 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። አርባምንጫ ከተማ ከሊጉ መውረዱ ይታወቃል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ37ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና መቀሌ 70 እንደርታን 3 ለ 0 አሸንፏል። ይህን ተከትሎም መቀሌ 70 እንደርታ ከአርባምንጭ ከተማ በመቀጠል ወደ ከፍተኛ ሊግ የወረደ ሁለተኛ ቡድን ሆኗል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ፋሲል ከነማን 1 ለ 0፣ ነገሌ አርሲ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 2 ለ 0 አሸንፈዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም