ቀጥታ፡
ስፖርት
ቼልሲ እና አርሰናል በካራባኦ ዋንጫ የሚያደርጉት የግማሽ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 14, 2026 15
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር የግማሽ ፍፃሜ መርሃ ግብር ቼልሲ እና አርሰናል ዛሬ ይጫወታሉ። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ይካሄዳል። በሩብ ፍጻሜው ቼልሲ ካርዲፍ ሲቲን ፣ አርሰናል ክሪስታል ፓላስን በማሸነፍ የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብተዋል። ቼልሲ የካራባኦ ዋንጫን አምስት ጊዜ አንስቷል። የለንደን ጎረቤቱ አርሰናል ሁለት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሆኗል። የምዕራብ ለንደኑ ክለብ ቼልሲ ለመጨረሻ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ የነበረው እ.አ.አ በ2014/15 የውድድር ዓመት ነው። የሰሜን ለንደኑ አርሰናል እ.አ.አ 1992/93 ለመጨረሻ ጊዜ ዋንጫውን አንስቷል። ቡድኖቹ በካራባኦ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም እርስ በእርስ ባደረጓቸው ሶስት ጨዋታዎች ሁለቱ ክለቦች በተመሳሳይ አንድ ጊዜ ሲያሸንፉ በቀሪው ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። እ.አ.አ በ2018 በተመሳሳይ በግማሽ ፍጻሜ ተገናኝተው አርሰናል በድምር ውጤት 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። መድፈኞቹ በፍጻሜው በማንችስተር ሲቲ 3 ለ 0 ተሸንፈው ዋንጫውን አጥተዋል። አዲሱ የቼልሲ ሊያም ሮሲኒየር የመጀመሪያ ጨዋታቸውን ዛሬ ያደርጋሉ። የሁለቱ ክለቦች የመልስ ጨዋታ ጥር 26 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ትናንት በካራባኦ ዋንጫ በተደረገው የመጀመሪያ ዙር የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 0 አሸንፏል።
የአፍሪካ ዋንጫን የወርቅ ጫማ ማን ይወስዳል?
Jan 14, 2026 33
በሞሮኮ አስተናጋጅነት ታህሳስ 12 ቀን 2018 ዓ.ም የተጀመረው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ወደ መገባደዱ ላይ ደርሷል። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ሴኔጋል ከግብጽ ምሽት አንድ ሰዓት፣ ናይጄሪያ ከሞሮኮ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ ለፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ተጠባቂ ናቸው።   በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ እስከ አሁን በተደረጉ 48 ጨዋታዎች 119 ግቦች ከመረብ ላይ አርፈዋል። በየጨዋታው በአማካይ 2 ነጥብ 48 ግቦችን ተቆጥረዋል። 119 ግቦች ኮትዲቯር ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ላይ ከተቆጠረው ተመሳሳይ የግብ መጠን ተስተካክሏል። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በውድድሩ ታሪክ በርካታ ግቦች የተቆጠሩበት ሆኖ እንደሚጠናቀቅ እርግጥ ነው። ጨዋታዎቹ በጎል የታጀቡ እና አዝናኝ እንቅስቃሴ ተደርጎባቸዋል።   ከዋንጫው ፉክክር ባልተናነሰ የኮከብ ግብ አስቆጣሪነቱ ጉዳይ የእግር ኳስ አፍቃሪያን ትኩረት ስቧል። በውድድሩ ላይ ድንቅ ጊዜ እያሳለፈ የሚገኘው የሞሮኮው የክንፍ መስመር ተጫዋች ብራሂም ዲያዝ በአምስት ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ይገኛል። የናይጄሪያው ቪክቶር ኦሲሜን እና የግብጹ መሐመድ ሳላህ በተመሳሳይ አራት ጎሎችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ይከተላሉ።   የሞሮኮው አዩብ ኤል ካቢ እና የናይጄሪያው አዴሞላ ሉክማን በተመሳሳይ ሶስት ግቦችን አስቆጥረዋል። ዛሬ ናይጄሪያ እና ሞሮኮ በሚያደርጉት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ የቪክቶር ኦሲሜን እና ብራሂም ዲያዝ ፍጥጫ ይጠበቃል።   ሴኔጋል ከግብጽ በሚያከናውኑት ሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር የግብጹ መሐመድ ሳላህ የሚጠበቅ ይሆናል። የወርቅ ጫማውን ማን ይወስዳል? ለሚለው ጥያቄ ቀሪ አራት ጨዋታዎች ምላሽ ይሰጣሉ።
ኃያላኑን ያገናኘው የአፍሪካ ዋንጫ ተጠባቂ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር
Jan 14, 2026 41
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ሴኔጋል ከግብጽ ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ በታንጀር ስታዲየም ይጫወታሉ። በሩብ ፍጻሜው ሴኔጋል ማሊን፣ ግብጽ ኮትዲቯርን በማሸነፍ የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብተዋል። ሁለቱ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለስድስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው አምስት ጨዋታዎች ሴኔጋል በሶስቱ ድል ሲቀናት ግብጽ ሁለት ጊዜ አሸንፋለች። እ.አ.አ በ1986 ግብጽ ባዘጋጀችው 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው ሴኔጋል በቲርኖ ዩም ጎል 1 ለ 0 አሸንፋለች። በሀገራቱ የእርስ በእርስ ግንኙነት ውስጥ በዋናነት የሚነሳው ካሜሮን እ.አ.አ በ2021 ባዘጋጀችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዋንጫ ለማንሳት የተፋለሙበት ነው። ሴኔጋል በመለያ ምት 4 ለ 2 በማሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካን ዋንጫ አንስታለች። ግብጽ ለመጨረሻ ጊዜ ሴኔጋልን በአፍሪካ ዋንጫው ያሸነፈችው እ.አ.አ በ2006 ባዘጋጀችው 25ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በግማሽ ፍጻሜው ተገናኝተው ግብጽ በአህመድ ሀሰን እና አሚር ዛኪ ግቦች 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፋለች። ማማዱ ኒያንግ ለሴኔጋል ብቸኛውን ጎል ያስቆጠረ ተጫዋች ነው። ግብጽ በፍጻሜው ኮትዲቯርን በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ውድድሩን ሰባት ጊዜ በማሸነፍ ስኬታማዋ ሀገር ናት። ከቅርብ ዓመታት በአፍሪካ እግር ኳስ ውስጥ ተፎካካሪነታቸው እያደገ የመጣው ሁለቱ ሀገራት ለፍጻሜው ለማለፍ ጠንካራ ፍልሚያ ያደርጋሉ። በሊቨርፑል ማልያ አንድ ላይ የተጫወቱት ሳዲዮ ማኔ እና መሐመድ ሳላህ በጨዋታው ላይ ልዩነት ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ናይጄሪያ ከሞሮኮ ምሽት አምስት ላይ በፕሪንስ ሙላይ የሚያደርጉት ጨዋታም ተጠባቂ ነው። ናይጄሪያ በሩብ ፍጻሜው አልጄሪያን፣ ሞሮኮ ካሜሮንን በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል። ሀገራቱ በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለስድስተኛ ጊዜ ነው። የመጀመሪያ ጨዋታቸውን ያደረጉት ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1976 በተካሄደው 10ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው። በምድብ ሁለት ተገናኝተው ሞሮኮ 3 ለ 1 አሸንፋለች። አህመድ ፋራስ፣ አብደላ ታዚ እና ላርቢ ቼባክ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሳሙኤል ኦጄቦዴ ለናይጄሪያ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሞሮኮ ጊኒን በማሸነፍ ብቸኛውን ዋንጫ በወቅቱ አንስታለች። እ.አ.አ በ1980 በናይጄሪያ በተካሄደው 12ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በግማሽ ፍፃሜው ተገናኝተው አዘጋጇ ናይጄሪያ በግማሽ ፍጻሜው በፍሊክስ ኦዎላቢ ግብ 1 ለ 0 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፋለች። በፍጻሜው ናይጄሪያ አልጄሪያን 3 ለ 0 በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ብሄራዊ ቡድኖቹ ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ2004 በቱኒዚያ በተካሄደው 24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነበር። በምድብ አራት ባደረጉት ጨዋታ በዩሱፍ ሃጂ ጎል ሞሮኮ 1 ለ 0 አሸንፋለች። ሁለቱ ሀገራት አጠቃላይ አምስት ጊዜ ተገናኝተው ሞሮኮ ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ ናይጄሪያ ሁለት ጊዜ ድል ቀንቷታል። ከ22 ዓመታት በኋላ በአህጉራዊው መድረክ የሚገናኙት ሀገራቱ ለተመልካች አዝናኝ እና ተመጣጣኝ ፉክክር ያሳያሉ ተብሎ ይጠበቃል። አራት ግቦችን ያስጠቆጠረው ቪክቶር ኦሲሜን ከናይጄሪያ እና አምስት ግቦችን ከመረብ ጋር በማገናኘት ኮከብ ግብ አግቢነቱን የሚመራው ብራሂም ዲያዝ ከሞሮኮ በጨዋታው ልዩነት ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል። የዛሬ ጨዋታ አሸናፊዎች ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም ዋንጫውን ለማንሳት ይፋለማሉ። ተሸናፊ ሀገራት ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ጥር 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይጫወታሉ። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በካራባኦ ዋንጫ ማንችስተር ሲቲ ድል ቀንቶታል
Jan 14, 2026 58
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሴይንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶዋን ሴሜንዮ በ53ኛው እና ራያን ቸርኪ በ98ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። በጨዋታው ላይ ማንችስተር ሲቲ ኢላማቸውን የጠበቁ የግብ ሙከራዎችን በሚገባ መጠቀሙ ባለድል አድርጎታል። በአንጻሩ ኒውካስትል ዩናይትድ ግልጽ የግብ እድሎችን አምክኗል። በጨዋታው ላይ አዲስ ፈራሚው ሴሜንዮ ጥሩ ብቃት ያሳየ ሲሆን የጨዋታው ኮከብ በመሆን ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ ወደ ፍጻሜ የማለፍ እድሉን አስፍቷል። በአንጻሩ የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ኒውካስትል ዩናይትድ ውጤቱን የመቀልበስ ጠንካራ የቤት ስራ ይጠብቀዋል። የሁለቱ ክለቦች የግማሽ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታ ጥር 27 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ሌላኛው የመጀመሪያ ዙር የካራባኦ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር በቼልሲ እና አርሰናል መካከል ነገ ይደረጋል።
ከማላጋ እስከ አፍሪካ ዋንጫ፤ የሞሮኮው አዲስ እንቁ ብራሂም ዲያዝ
Jan 13, 2026 112
  የግል ክህሎት፣ ፈጣን አስተሳሰቡ እና በጠባብ ክፍተቶች ውስጥ ሰብሮ የመግባት አቅሙ ሙገሳ እንዲጎርፍለት አድርጓል። አንድ ለአንድ ሲገናኝ ተከላካዮችን በፈጣን አካላዊ ቅልጥፍና እና በድንገት አቅጣጫ በመቀየር የሚያልፍበት መንገድ እንዲሁም የመፍጠር አቅሙ የተመልካቾችን ቀልብ የሚይዝ ነው። የአማካይ እና የአጥቂ መስመርን በማገናኘት እና በአስገራሚ ሁኔታ አጭር ኳሶችን በማቀበልም የተዋጣለት ተጫዋች ነው ማለት ይቻላል። በቦታ አያያዙ የእግር ኳስ ልኅቀቱ ከፍተኛ ነው የሚል አድናቆት ከእግር ኳስ ባለሙያዎች አግኝቷል። ኳስን ሲያንከባልልም ለዐይን ይስባል። ከክህሎቱ እና ከማራኪ እንቅስቃሴው ባለፈ ወደ ኋላ እየመለሰ ተከላካዮችን ያግዛል፣ ኳስ ይነጥቃል። ይህ ተጫዋች የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ክስተት የሆነው የሞሮኮው ብራሂም ዲያዝ ነው። የ26 ዓመቱ የሪያል ማድሪድ የክንፍ መስመር ተጫዋች ዲያዝ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ አምስት ጨዋታዎችን አድርጎ አምስት ግቦችን በማስቆጠር የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። አዘጋጇ ሞሮኮ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ መክፈቻ ኮሞሮስን 2 ለ 0 ስታሸንፍ የውድድሩን የመጀመሪያ ግብ አስቆጥሯል።   ብራሂም አብዱልቃድር ዲያዝ የተወለደው እ.አ.አ ኦገስት 3 ቀን 1999 በስፔን ማላጋ ግዛት ነው። እናቱ ስፔናዊ አባቱ ሞሮኳዊ ናቸው። ዲያዝ ያደገው በማላጋ ነው። እግር ኳስንም በአንዳሉሺያዊቷ ከተማ ሲጫወት ቆይቷል። በ16 ዓመቱ ካደገበት ማላጋ በመውጣት እ.አ.አ በ2015 ወደ ማንችስተር ሲቲ ወጣት አካዳሚ በ200 ሺህ ፓውንድ ወጪ ተዘዋወረ። ዲያዝ እ.አ.አ ሴፕቴምበር 21 ቀን 2016 በካራባኦ ካፕ (በቀድሞ አጠራሩ ሊግ ካፕ) ማንችስተር ሲቲ ከስዋንሲ ሲቲ ባደረገው ጨዋታ በ80ኛው ደቂቃ በኬሌቺ ኢናቺዩ ተቀይሮ በመግባት ለውኃ ሰማያዊዎቹ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የመጀመሪያውን ጨዋታ ካደረገ ከሶስት ቀናት በኋላ ከማንችስተር ሲቲ ጋር ለሶስት ዓመታት የሚያቆየውን ፕሮፌሽናል ኮንትራት ተፈራርሟል። እ.አ.አ ኖቬምበር 21 ቀን 2017 ማንችስተር ሲቲ ከፌይኖርድ ሮተርዳም ጋር ባደረገው የሻምፒዮናስ ሊግ ጨዋታ ላይ የመጀመሪያ የአውሮፓ መድረክ ጨዋታውን ማድረግ ችሏል። በወቅቱ ብራሂም ስተርሊን መደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በጭማሪ ሰዓት ላይ ነበር ተቀይሮ የገባው። ዲያዝ በውኃ ሰማያዊዎቹ ማልያ ቋሚ አሰላለፍ ውስጥ ገብቶ የተጫወተው እ.አ.አ ዲሴምበር 19 ቀን 2017 ነው። ማንችስተር ሲቲ ከሌስተር ሲቲ በካራባኦ ካፕ ጨዋታ ላይ ለ88 ደቂቃዎች ተሰልፎ ተጫውቷል።   እ.አ.አ ጃንዋሪ 20 ቀን 2018 ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 3 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። በወቅቱ ማንችስተር ሲቲ የሊጉን ዋንጫ ያነሳ ሲሆን፤ በውድድር ዓመቱ አራት ጨዋታዎች ላይ ብቻ ተሳትፎ ያደረገው ብራሂም ዲይዝ የሜዳሊያ ሽልማት አግኝቷል። እ.አ.አ ኦገስት 5 ቀን 2018 ማንችስተር ሲቲ ቼልሲን 2 ለ 0 ባሸነፈበት የኮሙዩኒቲ ሺልድ ጨዋታ ላይ በፊል ፎደን ተቀይሮ በመግባት ለ15 ደቂቃዎች ተጫውቷል። ዲያዝ እ.አ.አ 2018/19 ማብቂያ ላይ ማንችስተር ሲቲ ፉልሃምን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የመጀመሪያ ግቦቹን ለሲቲ አስቆጥሯል። በማንችስተር ሲቲ ያለው ውል እ.አ.አ 2019 ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ወቅት ስሙ ከዝውውር ጋር በስፋት ይነሳ ነበር። ዲያዝ እ.አ.አ ጥር 2019 በ17 ሚሊዮን ዩሮ ከማንችስተር ሲቲ ወደ ሪያል ማድሪድ ተዘዋወረ። ለስድስት ዓመታት የሚያቆየውን ውልም ፈርሟል። የክንፍ ተጫዋቹ የመጀመሪያ ጨዋታውን በነጮቹ ማልያ ያደረገው እ.አ.አ ጥር 9 ቀን 2019 ሪያል ማድሪድ ሌጋኔን በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ 3 ለ 0 ባሸነፈበት ወቅት ነው። ከአራት ቀናት በኋላ በስፔን ላሊጋ ሪያል ማድሪድ ሪያል ቤቲስን 2 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ ተቀይሮ በመግባት በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የመጀመሪያ ግቡን ለማስቆጠር ሶስት ወራትን ጠብቋል። እ.አ.አ ግንቦት 12 ቀን 2019 ሪያል ማድሪድ በላሊጋው በሪያል ሶሲዬዳድ 3 ለ 1 ሲሸነፍ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በወቅቱ ዲያዝ ስድስት ጨዋታዎች ላይ በላሊጋው የተጫወተ ሲሆን፤ በመጀመሪያ ዓመቱ የሊጉን ዋንጫ አንስቷል። ሪያል ማድሪድ እ.አ.አ በ2021/21 የውድድር ዓመት ብራሂም ዲያዝ ወደ ኤሲ ሚላን በውሰት ማምራቱን ይፋ አደረገ። ዲያዝ ሚላን እ.አ.አ መስከረም 27 ቀን 2020 ክሮቶኔን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ የመጀመሪያ ግቡን ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ ግንቦት 2021 ኤሲ ሚላን ጁቬንቱስን 3 ለ 0 ሲያሸንፍ ያስቆጠረው ግብም ተጠቃሽ ነው። ዲያዝ በኤሲ ሚላን የውሰት ውሉ ሲያበቃ በድጋሚ ለሁለት ዓመታት በውሰት የሚቆይበት ስምምነት ሪያል ማድሪድ ከጣልያኑ ክለብ ጋር የተፈራረመ ሲሆን፤ ውሉ ሚላን ተጫዋቹን የማቆየት መብት ሰጥቶታል። እ.አ.አ መስከረም 15 ቀን 2021 ኤሲ ሚላን በሻምፒዮንስ ሊጉ የ3 ለ 2 ሽንፈት ሲያስተናግድ የመጀመሪያ የአውሮፓ መድረክ ግቡን አስቆጥሯል። በ2023 ኤሲ ሚላን ቶተንሃም ሆትስፐርስን በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ጥሎ ማለፍ 1 ለ 0 ሲያሽንፍ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ በ2023 ሰኔ ወር ላይ ሪያል ማድሪድ ዲያዝ ከኤሲ ሚላን የሶስት ዓመታት የውሰት ቆይታ በኋላ ወደ ክለቡ መመለሱን አሳውቋል። ተጫዋቹ በኤሲ ሚላን ቆይታው 91 ጨዋታዎችን አድርጎ 13 ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ዲያዝ ወደ ሪያል ማድሪድ ከተመለሰ በኋላ ኮንትራቱን እስከ 2027 አራዝሟል። እ.አ.አ መስከረም 27 ቀን 2023 ወደ ክለቡ ከተመለሰ በኋላ ሪያል ማድሪድ ላስ ፓልማስን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ ግብ አስቆጥሯል።   የክንፍ መስመር ተጫዋቹ ሪያል ማድሪድ በሀገር ውስጥ እና በአውሮፓ መድረክ በሚያደርጋቸው ጨዋታዎች ላይ ግብ በማስቆጠር እና ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል። ዲያዝ እስከ አሁን ለሪያል ማድሪድ ባደረጋቸው 129 ጨዋታዎች 20 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከነዚህም ውስጥ 13ቱ በላሊጋው ያስቆጠራቸው ናቸው። ከክለብ ወጣ ስንል የተጫዋቹን የብሔራዊ ቡድን ቆይታ እናገኛለን። ዲያዝ በታዳጊነቱ በተለያዩ የእድሜ እርከኖች ለስፔን ወጣት ቡድኖች ተጫውቷል። እ.አ.አ በ2016/17 የውድድር ዘመን ለስፔን ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በ16 ዓመቱ ተሰልፎ መጫወት ችሏል። በተለይም አዘርባጃን እ.አ.አ በ2017 ባዘጋጀችው 15ኛው የአውሮፓ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ላይ ያሳየው ድንቅ ብቃት አድናቆት አስችሮታል። በዚያ ቀጥለው በነበሩ ዓመታትም ለስፔን ከ19 እና ከ21 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድኖች ተጫውቷል። ብራሂም ዲያዝ በስፔን ታዳጊና ወጣት ቡድኖች ላይ በአጠቃላይ 28 ጨዋታዎችን አድርጎ ስድስት ግቦችን አስቆጥሯል። የስፔን ታዋቂ የስፖርት ጋዜጣ ማርካ እ.አ.አ ጥር 23 ቀን 2023 ለሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን መጫወት ማቀዱን የሚመለከት ዘገባ ይዞ ወጥቷል። ከዜግነቱ ጋር በተያያዘ ያሉ አንዳንድ የአስተደዳር ጉዳዮች በወቅቱ መፍትሄ አግኝተዋል። ይሁንና ኮትዲቯር እ.አ.አ በ2023 ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሞሮኮው አሰልጣኝ ዋሊድ ሬግራጉዊ ከተጫዋቹ ጋር በተደረገ የቅድሚያ ስምምነት ለተጫዋቹ ጥሪ አልተደረገለትም። ዲያዝ እ.አ.አ መጋቢት 10 ቀን 2024 ለሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለሀገሪቷ ብሔራዊ መጫወት እንደሚፈልግ በይፋ ማሳወቁን ማርካ በወቅቱ ዘግቧል። ጥያቄውም ተቀባይነት አገኘ። በወቅቱ የሞሮኮ አሰልጣኝ ዋሊድ ሬግራጉዊ ብሔራዊ ቡድኑ ከአንጎላ እና ሞሪታኒያ ጋር ለነበረበት የወዳጅነት ጨዋታ ለዲያዝ ጥሪ አድርገውለታል። እ.አ.አ መጋቢት 22 ቀን 2024 ሞሮኮ አንጎላን 1 ለ 0 ባሸነፈችበት ጨዋታ ለብሔራዊ ቡድኑ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። እ.አ.አ ጥቅምት 6 ቀን 2024 ሞሮኮ ለ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከጋቦን ጋር ባደረገችው ጨዋታ 4 ለ 1 ስታሸንፍ የመጀመሪያ ግቡን ለሞሮኮ ማስቆጠር ቻለ። እ.አ.አ ሕዳር 15 ቀን 2024 ሞሮኮ በማጣሪያው ጋቦንን 5 ለ 1 ስትረታ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ማሳረፍ ችሏል። ከሶስት ቀናት በኋላ ሞሮኮ ከሌሴቶ ጋር ባደረገችው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታ 7 ለ 0 ስታሸንፍ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር በሀገሩ ማልያ የመጀመሪያ ሀትሪኩን ሰርቷል። እ.አ.አ ጥቅምት 2025 ሞሮኮ ራባት ላይ ኮንጎ ሪፐብሊክን 1 ለ 0 በማሸነፍ በስፔን ከዚህ ቀደም በብሔራዊ ቡድን ደረጃ ተይዞ የነበረውን 15 ተከታታይ ጨዋታዎችን የማሸነፍ ክብረ ወሰን በመስበር ወደ 16 ማድረስ ችላለች። በዚህ ታሪካዊ ጨዋታ ላይ ዲያዝ ተሰልፎ ተጫውቷል። የሞሮኮ ተከታታይ የማሸነፍ ጉዞ 19 ጨዋታዎች ደርሶ የነበረ ሲሆን በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከማሊ ጋር አንድ አቻ ስትለያይ አብቅቷል።   ሞሮኮ ለ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በማጣሪያ ብታልፍም አስቀድማ ውድድሩን እንድታዘጋጅ እድል አግኝታ የነበረው ጊኒ በዝግጅት ማነስ ምክንያት በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ከሁለት ዓመት በፊት አዘጋጅነቷ ተነጥቆ ለሞሮኮ ተሰጥቷል። ሞሮኮ የዘንድሮውን ውድድር በደማቅ ሁኔታ እያካሄደች ትገኛለች። በውድድሩ ላይ ጎልተው ከታዩ ተጫዋቾች መካከል ብራሂም ዲያዝ ተጠቃሽ ነው። በአፍሪካ ዋንጫው እስከ አሁን ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። በተሰለፈባቸው በእያንዳዱ ጨዋታዎች ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ለሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን በአምስት የአፍሪካ ዋንጫ ተከታታይ ጨዋታዎች ግብ ያስቆጠረ የመጀመሪያው ተጫዋች በመሆን አዲስ ታሪክ ጽፏል። ሞሮኮ በሩብ ፍጻሜው ማሊን 2 ለ 0 ስታሸንፍ የመጀመሪያውን ጎል አስቆጥሯል። ሀገሩ ወደ ግማሽ ፍጻሜ እንድታልፍ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱንም እየመራ ይገኛል። ሞሮኮ በዚሁ ግስጋሴዋ ከቀጠለች ዲያዝ የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ እና ኮከብ ተጫዋች የመሆን እድሉ ሰፊ ነው። ሞሮኮ በግማሽ ፍጻሜው ከናይጄሪያ ጋር ረቡዕ ጥር 6 ቀን 2018 ዓ.ም በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ታደርጋለች። ዲያዝ በዚህ ጨዋታ ላይ ልዩነት ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል። አንዳንድ የእግር ኳስ ተንታኞች ብራሂም ዲያዝ እ.አ.አ በ2026 ወጥነት ያለው ብቃት ማሳየት ከቻለ የአፍሪካ ኮከብ ተጫዋችነት ሽልማቱን የሚወስድበት የለም እያሉ ይገኛሉ። ሞሮኳውያን በተጫዋቹ ፍቅር ልባቸው ከንፏል። በየጨዋታው ዲያዝ ዲያዝ እያሉ ከፍተኛ ድጋፍ እና ሙገሳ እየሰጡት ይገኛሉ። እሱም በድንቅ ብቃቱ ምላሽ እየሰጣቸው ነው። በተወለደበት ማላጋ ከተማ የጀመረው የእግር ኳስ ሕይወት በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የበለጠ አብቧል። የሞሮኮው አዲሱ ኮከብ ብራሂም ዲያዝ ቀጣይ የእግር ኳስ ሕይወት በስኬት እና በድል የደመቀ እንደሚሆን ከአሁኑ ድንቅ ብቃቱ ተነስቶ መናገር ይቻላል።
በኤፍኤ ካፕ ሊቨርፑል ከባርንስሌይ ጋር ይጫወታል
Jan 12, 2026 94
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ የሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር ሊቨርፑል ከባርንስሌይ ጋር ዛሬ ጨዋታውን ያደርጋል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ምሽት 4 ሰዓት ከ45 ላይ በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ይካሄዳል። ሊቨርፑል የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ለስምንት ጊዜ በማንሳት ስኬታማ ከሚባሉ ክለቦች አንዱ ነው። በእንግሊዝ ሶስተኛ የሊግ የውድድር እርከን (ሊግ ዋን) የሚገኘው ባርንስሌይ አንድ ጊዜ ውድድሩን አሸንፏል። ሁለቱ ክለቦች በኤፍኤ ካፕ ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው።   እ.አ.አ 1985 ለመጀመሪያ ጊዜ ተገናኝተው ሊቨርፑል 4 ለ 1 አሸንፏል። እ.አ.አ በ2008 16 ውስጥ ባደረጉት ጨዋታ ባርንስሌይ ሊቨርፑልን ሳይጠበቅ 2 ለ 1 በማሸነፍ ወደ ሩብ ፍጻሜ ገብቷል። ክለቦቹ ከ18 ዓመታት በኋላ በመድረኩ ይገናኛሉ። ሊቨርፑል ጨዋታውን የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት አግኝቷል። የኤፍኤ ካፕ የሶስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ አራተኛ ቀኑን ያስቆጠረ ሲሆን ነገ ይጠናቀቃል። 155 ዓመታትን ያስቆጠረው ኤፍኤ ካፕ የዓለም አንጋፋው የክለቦች ውድድር ነው።
ማንችስተር ዩናይትድ ከኤፍኤ ካፕ ውድድር ተሰናበተ
Jan 11, 2026 141
አዲስ አበባ፤ ጥር 3/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ የሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር ብራይተን ማንችስተር ዩናይትድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብራጃን ግሩዳ እና ዳኒ ዌልቤክ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ቤንጃሚን ሼስኮ ለዩናይትድ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የማንችስተር ዩናይትዱ ሼ ሌሲ በ89ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ለብራይተን አንድ ጎል ያስቆጠረው ብራጃን ግሩዳ የጨዋታ ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ ብራይተን ወደ አራተኛ ዙር አልፏል። የ13 ጊዜ የኤፍኤ ካፕ አሸናፊ ማንችስተር ዩናይትድ በሶስተኛ ዙር ከውድድሩ ተሰናብቷል። ዛሬ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ አርሰናል ፖርትስማውዝን 4 ለ 1 አሸንፏል። በፍራተን ፓርክ በተካሄደው ጨዋታ ጋብርኤል ማርቲኔሊ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሲሰራ የፖርትስማውዙ አንድሬ ዶዜል በራሱ ላይ ቀሪዋን ግብ ለአርሰናል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ኮልቢ ቢሾፕ ለፖርትስማውዝ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አስቆጥሯል። 14 ጊዜ ዋንጫ በማንሳት የውድድሩ ስኬታማ ክለብ የሆነው አርሰናል ወደ አራተኛ ዙር አልፏል። ሶስተኛ ቀኑን ያስቆጠረው የኤፍኤ ካፕ የሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር እስከ ጥር 5 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የወቅቱ የኤፍኤ ካፕ አሸናፊ ክሪስታል ፓላስ ትናንት በማክስፊልድ 2 ለ 1 ተሸንፎ ከውድድሩ ውጪ ሆኗል። 155 ዓመታትን ያስቆጠረው ኤፍኤ ካፕ የዓለም አንጋፋው የክለቦች ውድድር ነው።
በኤል ክላሲኮ ደርቢ ባርሴሎና ሪያል ማድሪድን በማሸነፍ የስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫን አነሳ
Jan 11, 2026 111
አዲስ አበባ፤ ጥር 3/2018(ኢዜአ)፦ በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ የፍጻሜ ጨዋታ ባርሴሎና ሪያል ማድሪድን 3 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በሳዑዲ አረቢያ ኪንግ አብዱላህ ስፖርትስ ሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ራፊኒያ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሮበርት ሌዋንዶስኪ ቀሪዋን ጎል ለባርሴሎና ከመረብ አሳርፏል። ቪኒሺየስ ጁኒየር እና ጎንዛሎ ጋርሺያ ለሪያል ማድሪድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በ91ኛው ደቂቃ የባርሴሎናው ፍራንኪ ዲ ዮንግ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። የባርሴሎናው ራፊኒያ በውድድር ዓመቱ በሁሉም ውድድሮች ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ 11 ከፍ አድርጓል። በጨዋታው ባርሴሎና በኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ሁለቱም ቡድኖች በቁጥር ተቀራራቢ የግብ እድሎችን ፈጥረዋል። ጨዋታው አዝናኝ እና ሳቢ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ባርሴሎና ለ16ኛ ጊዜ የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫን አንስቷል። የባለፈው ዓመት ክብሩንም ማስጠበቅ ችሏል። ባርሴሎና ለበርካታ ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ ስኬታማ ክለብ ነው። ሪያል ማድሪድ 13 ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት ይከተላል። የስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በስፔን ላሊጋ እና በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ በተመሳሳይ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን የያዙ ክለቦች የሚሳተፉበት ውድድር ነው።
የስፖርት ቱሪዝም መጠናከር ለኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መነቃቃት ፋይዳው የጎላ ነው
Jan 11, 2026 104
ደብረብርሃን ፤ጥር 3/2018 (ኢዜአ) ፡- ስፖርት ጤናማና አምራች ዜጋን በመፍጠር የአካባቢውን ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ምርታማነት ለማሳደግ የጎላ ፋይዳ አለው ሲሉ የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በደሉ ውብሸት ገለጹ። የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ 2018 የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድሮች ዛሬ በደብረብርሃን ከተማ ተካሂደዋል።   ውድድሮቹም የ6 ኪሎ ሜትር የሴቶችና ወንዶች ሩጫ እና የ22 ኪሎ ሜትር የዱላ ቅብብልን ያካተተ ነው። የደብረብርሃን ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት በእለቱ እንደገለጹት ስፖርት ጤናማና አምራች ዜጋን በመፍጠር ለአካባቢው ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ምርታማነት እድገት የጎላ ፋይዳ አለው። በተጨማሪም ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ ስፖርተኞችንና ተመልካቾችን በማገናኘት ለማህበራዊ ትስስር መጠናከር አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። በደብረ ብርሃን የተካሄደው የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያም የከተማዋን እድገት፣ የመስህብ ስፍራዎችና ጸጋዎችን ለማስተዋወቅ መልካም እድል የሚፈጥር በመሆኑ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም መምሪያ የቅርስ ጥበቃና ቱሪዝም ቡድን መሪ አቶ አክሊል ጌታቸው እንዳሉት ከተማዋ ያላት የአየር ንብረት ለስፖርታዊ ውድድሮች አመቺ ነው።   ዛሬ የተካሄደው የስፖርት ውድድርም ወንድማማችነትን ለማጠናከርና ያሉ የተፈጥሮ ፀጋዎችን ለማስተዋወቅ የሚያግዝ በመሆኑ አዘጋጆቹን አመስግነዋል። የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የኮሙኒኬሽን ሀላፊ ወይዘሮ ሃና ገብረስላሴ በበኩላቸው ዛሬ በደብረ ብርሃን ከተማ ህፃናትን፣ ወጣቶችንና ታዋቂ አትሌቶችን ያሳተፈ ውድድር መካሄዱን ገልጸዋልⵆ ውድድሩም የ6 ኪሎ ሜትር የሴቶችና ወንዶች ሩጫ እና የ22 ኪሎ ሜትር የዱላ ቅብብልን ያካተተ እንደነበር አንስተዋል። በ6 ኪሎ ሜትር የወንዶች ሩጫ ውድድር 1ኛ የወጣው ስጦታው ሰማኸኝ እንዳለው እንደዚህ ያለ ውድድር ያልታወቁ አትሌቶች የሚታዩበት በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል።
የኤፍኤ ካፕ ባለ ብዙ ክብሩ አርሰናል ከፖርትስማውዝ ይጫወታል 
Jan 11, 2026 118
አዲስ አበባ፤ ጥር 3/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ የሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር ዛሬ ሶስተኛ ቀኑን ይዟል። ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በፍራተን ፓርክ ስታዲየም ፖርትስማውዝ ከአርሰናል ይጫወታሉ። በእንግሊዝ ሁለተኛ ዲቪዚዮን (ሻምፒዮንሺፕ) የሚጫወተው ፖርትስማውዝ የሁለት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ነው። አርሰናል 14 ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት የውድድሩ ስኬታማ ክለብ ነው። ሁለቱ ክለቦች በኤፍኤ ካፕ ሲገናኙ የአሁኑ ለአምስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው አራት ጨዋታዎች አርሰናል ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። አርሰናል ጨዋታውን የማሸነፍ ሰፊ ግምት አግኝቷል። በሌላኛው መርሃ ግብር ማንችስተር ዩናይትድ ከብራይተን ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ በኦልትራፎርድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ዩናይትድ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን 13 ጊዜ አንስቷል። የብራይተን ትልቁ ውጤት እ.አ.አ በ1982/83 ለፍጻሜ ደርሶ በዛሬ ተጋጣሚው ተሸንፎ ዋንጫ ያጣበት አጋጣሚ ነው። ሁለቱ ክለቦች ከዚህ ቀደም ሶስት ጊዜ በውድድሩ ተገናኝተው ማንችስተር ዩናይትድ ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። ብራይተን በዩናይትድ ላይ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ዌስትሃም ዩናይትድ ከኪውፒአር፣ ደርቢ ካውንቲ ከሊድስ ዩናይትድ እና ስዋንሲ ሲቲ ከዌስትብሮም ዛሬ ከሚደረጉ የኤፍኤ ካፕ ጨዋታዎች መካከል ይጠቀሳሉ። ኤፍኤ ካፕ እ.አ.አ በ1871 መጀመሩን መረጃዎች ያመለክታሉ። 155 ዓመታትን ያስቆጠረው ኤፍኤ ካፕ የዓለም አንጋፋው የክለቦች ውድድር ነው።
ተጠባቂው የኤል ክሊሳኮ ደርቢ በስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ፍጻሜ
Jan 11, 2026 82
አዲስ አበባ፤ጥር 3 / 2018 (ኢዜአ)፦በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ባርሴሎና እና ሪያል ማድሪድ ዛሬ የሚያደርጉት የፍጻሜ ጨዋታ በጉጉት ይጠበቃል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 4 ሰዓት በሳዑዲ አረቢያ ኪንግ አብዱላህ ስፖርትስ ሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። ባርሴሎና በግማሽ ፍጻሜው አትሌቲኮ ቢልባኦን 5 ለ 0 እንዲሁም ሪያል ማድሪድ አትሌቲኮ ማድሪድን 2 ለ 1 አሸንፈዋል። የባርሴሎና እና ሪያል ማድሪድ ታሪካዊ ተቀናቃኝነት ከ120 ዓመታት በላይ የዘለቀ ነው። ሁለቱ ክለቦች እ.አ.አ በ1902 ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ባርሴሎና 3 ለ 1 አሸንፏል። ቡድኖቹ የወዳጅነት ጨዋታዎችን ጨምሮ እስከ አሁን 303 ጊዜ እርስ በእርስ ተገናኝተዋል። ባርሴሎና 128 ጊዜ ሲያሸንፍ ሪያል ማድሪድ 111 ጊዜ ድል ቀንቶታል። 64 ጊዜ አቻ ወጥተዋል። ሁለቱ ክለቦች በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ለፍጻሜ ሲገናኙ የዛሬው ለ18ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 16 ጨዋታዎች ሪያል ማድሪድ ዘጠኝ ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል።ባርሴሎና ስድስት ጊዜ ባለድል ሆኗል። ሁለት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥተዋል (ውድድሩ የደርሶ መልስ ጨዋታ ፎርማት በነበረው ወቅት)። አምና ሁለቱ ክለቦች በፍጻሜው ተገናኝተው ባርሴሎና 3 ለ 2 በማሸነፍ የዋንጫው ባለቤት መሆኑ የሚታወስ ነው። ቡድኖች የስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫን ለበርካታ ጊዜ ያነሱ ክለቦች ናቸው። ባርሴሎና 15 ጊዜ በማንሳት ቀዳሚነቱን ሲይዝ ሪያል ማድሪድ 13 ጊዜ አሸንፏል። በጉዳይ ላይ የሚገኘው የሪያል ማድሪዱ አጥቂ ኪሊያን እምባፔ በቡድኑ ስብስብ ውስ መካከቱ ለለሎስ ብላኮንሶቹ መልካም ዜና ሆኗል። የ42 ዓመቱ ሆዜ ሉዊስ ሞንቴሮ የሁለቱን ቡድኖች ተጠባቂ ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። የስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በስፔን ላሊጋ እና በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ በተመሳሳይ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን የያዙ ክለቦች የሚሳተፉበት ውድድር ነው።
ግብጽ የወቅቱን የአፍሪካ ዋንጫ ባለቤት ኮትዲቯር በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቀለች
Jan 11, 2026 120
አዲስ አበባ፤ ጥር 2 /2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ግብጽ ኮትዲቯርን 3 ለ 2 አሸንፋለች። ማምሻውን በአጋዲር ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኦማር ማርሙሽ፣ ራሚ ራቢያ እና መሐመድ ሳላህ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጉዌላ ዱዌ እና የግብጹ አህመድ አቡ ኤል ፎቱህ በራሱ ላይ ለኮትዲቯር ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ግብጽ ግልጽ የግብ እድሎችን በመፍጠር፣ ኮትዲቯር በኳስ ቁጥጥር የተሻሉ ነበሩ። ኮትዲቯር በጨዋታው ማብቂያ ላይ ተጭና ብትጫወትም ግብ ማስቆጠር አልቻለችም። የግብጹ መሐመድ ሳላህ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ አራት ከፍ አድርጓል። ድሉን ተከትሎ ግብጽ ግማሽ ፍጻሜ የገባች የመጨረሻዋ ሀገር ሆናለች። በግማሽ ፍጻሜው ከሴኔጋል ጋር የምታደርገው ጨዋታ ከወዲሁ ትኩረትን ስቧል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ኮትዲቯር የአፍሪካ ዋንጫ ክብሯን የመጠበቅ ጉዞዋ ሩብ ፍጻሜው ላይ ተገቷል። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ናይጄሪያ ከአዘጋጇ ሞሮኮ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ረቡዕ ጥር 6 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳሉ።
ኢትዮጵያ በዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቀቀች
Jan 10, 2026 169
አዲስ አበባ፤ ጥር 2 /2018 (ኢዜአ)፦ 46ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ማምሻውን በአሜሪካ ፍሎሪዳ ተካሄዷል። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በአምስት ርቀቶች በሁለቱም ጾታዎች በአጠቃላይ 20 አትሌቶችን አሳትፋለች። 10 ኪሎ ሜትር አዋቂ ወንዶች፣ 10 ኪሎ ሜትር አዋቂ ሴቶች፣ ከ20 ዓመት በታች ወንዶች 8 ኪሎ ሜትር፣ ከ20 ዓመት በታች ሴቶች 6 ኪሎ ሜትር እና ድብልቅ ሪሌይ (4 በ 2 ኪሎ ሜትር) ኢትዮጵያ የተሳተፈችባቸው ርቀቶች ናቸው። የዛሬ ውድድሮችን ተከትሎ ኢትዮጵያ በሶስት የወርቅ፣ ሁለት የብር እና ሁለት የነሐስ በድምሩ ሰባት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ኬንያን ተከትላ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ከ20 ዓመት በታች ሴቶች የስድስት ኪሎ ሜትር ውድድር አትሌት ማርታ ዓለማየሁ በ18 ደቂቃ 52 ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት ለኢትዮጵያ በሻምፒዮናው የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። ኢትዮጵያ በአዋቂ የ10 ኪሎ ሜትር ወንዶች እና ሶሴቶች በቡድን ሁለት የወርቅ ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በአዋቂ 10 ኪሎ ሜትር ወንድ ፍጻሜ አትሌት በሪሁ አረጋዊ ሁለተኛ በመውጣት የብር ሜዳሊያ አግኝቷል። አትሌት ወሰኔ አሰፋ ከ20 በታች ሴቶች የስድስት ኪሎ ሜትር ውድድር ሁለተኛ በመውጣት የብር ሜዳሊያ ባለቤት ሆናለች። በ10 ኪሎ ሜትር ሴቶች አትሌት ሰናይት ጌታቸው እና በድብልቅ ሪሌይ (ዱላ ቅብብል) የነሐስ ሜዳሊያዎች ተገኝተዋል። ኬንያ ሶስት የወርቅ፣ አራት የብር እና ሁለት የነሐስ በድምሩ ዘጠኝ ሜዳሊያዎችን በማግኘት አንደኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ዩጋንዳ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። አውስትራሊያ፣ ፈረንሳይ፣ ጃፓን እና አሜሪካ ሌሎች ሜዳሊያ ሰንጠረዥ ውስጥ የገቡ ሀገራት ናቸው። ኢትዮጵያ በሻምፒዮና ተሳትፎ ታሪኳ የዘንድሮውን ጨምሮ 112 የወርቅ፣ 123 ብር እና 67 የነሐስ በድምሩ 302 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ከኬንያ በመቀጠል ስኬታማዋ ሀገር ናት። ኬንያ የዘንድሮውን ጨምሮ ኬንያ 160 ወርቅ፣ 114 የብር እና 80 የነሐስ በድምሩ 354 ሜዳሊያዎችን በማግኘት የበላይነቱን ይዛለች።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም