ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ቼልሲ ሊያም ሮሲኒየርን አሰናበተ
Apr 22, 2026 271
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፦ የምዕራብ ለንደኑ ክለብ ቼልሲ ዋና አሰልጣኙን ሊያም ሮሲኒየርን ከኃላፊነት ማሰናበቱን በይፋ አስታውቋል። አሰልጣኙ በስታምፎርድ ብሪጅ በነበራቸው ቆይታ ክለቡን መምራት የቻሉት ለአራት ወራት ብቻ ሲሆን፣ ይህ ውሳኔ የተላለፈው ቡድኑ እያሳየ ባለው እጅግ ደካማ ውጤት ምክንያት መሆኑን ቢቢሲ ክለቡን ዋቢ በማድረግ ዘግቧል። በሮሲኒየር መሪነት ቼልሲ ካለፉት ዘጠኝ የፕሪምየር ሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው በአንዱ ብቻ ሲሆን፣ በተለይም ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ቡድኑ ምንም አይነት ግብ ሳያስቆጥር መሸነፉ ለአመራሮቹ ትዕግስት ማጣት ዋነኛ ምክንያት መሆኑ ተገልጿል። ቼልሲ ትናንት በሊጉ በብራይተን 3 ለ 0 መሸነፉ ይታወቃል። ሮሲኒየር የስድስት ዓመት ተኩል ረጅም ኮንትራት ፈርመው ወደ ክለቡ ቢመጡም፣ ቼልሲን በደረጃ ሰንጠረዡ ወደ ሰባተኛ ደረጃ ዝቅ ማድረጋቸው እና የቻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ እድላቸውን አደጋ ላይ መጣላቸው ለስንብቱ ምክንያት ሆኗል። ክለቡ ለሮሲኒየር እና ለረዳቶቻቸው በቆይታቸው ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋናውን አቅርቧል። በመጪው እሁድ ቼልሲ ከሊድስ ዩናይትድ ጋር ለሚያደርገው የኤፍ ኤ ካፕ (FA Cup) የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ፣ ካሉም ማክፋርሌን ቡድኑን በጊዜያዊ አሰልጣኝነት እንደሚመሩ ክለቡ አስታውቋል። ቼልሲ በአሁኑ ወቅት ቋሚ አሰልጣኝ ለመቅጠር ጥረት እያደረገ ሲሆን፣ ይህም በባለቤቱ ቶድ ቦህሊ ዘመን አምስተኛው አሰልጣኝ እንደሚሆን ቢቢሲ ዘግቧል።
አትሌት ገመኔ ማሚቴ ምትኩ በተከለከለ አበረታች ቅመም ምክንያት የስድስት ዓመት እገዳ ተጣለባት
Apr 22, 2026 177
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን አትሌት ገመኔ ማሚቴ ቱኩ የተከለከሉ አበረታች ቅመሞችን (Doping) ተጠቅማ በመገኘቷ የስድስት ዓመት የእገዳ ቅጣት እንደተጣለባት አስታወቀ። ባለስልጣኑ በሁለት የተለያዩ ውድድሮች ላይ ባካሄዳቸው ምርመራዎች፣ አትሌቷ ኤሪትሮፖይቲን (EPO) እና ዴክሳሜታሶን (Dexamethasone) የተባሉ የተከለከሉ ንጥረ ነገሮችን መጠቀምዋን ማረጋገጡን አመልክቷል። በዚህም መሠረት አትሌት ገመኔ ማሚቴ ቱኩ ጊዜያዊ እገዳ ከተጣለባት ጥቅምት 2 ቀን 2018 ዓ.ም (November 11, 2025) ጀምሮ ለስድስት ዓመታት የሚጸና፣ በማንኛውም ስፖርታዊ ውድድር እንዳትሳተፍ እገዳ መጣሉን ገልጿል። በተጨማሪም አትሌቷ ከግንቦት 3 ቀን 2017 ዓ.ም (May 11, 2025) ጀምሮ በተካሄዱ የተለያዩ ውድድሮች ያስመዘገበቻቸው ውጤቶች በሙሉ እንዲሰረዙ ተወስኗል። ይህም ሜዳሊያዎችን፣ የማዕረግ ስሞችን፣ ደረጃዎችን እና የሽልማት ገንዘቦችን መመለስን እንደሚጨምር ነው ባለስልጣኑ ያስታወቀው። በቀጣይም በሀገሪቱ በየደረጃው የሚደረገው የምርመራና ቁጥጥር ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተመልክቷል። የኢትዮጵያ የፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን የስፖርት አበረታች ቅመሞችን በመጠቀምም ሆነ በተለያየ መልኩ የፀረ-አበረታች ቅመሞች የህግ ጥሰት በሚፈጽሙ አትሌቶችና ከጀርባ ሆነው በሚያበረታቱ ሌሎች ግለሰቦች ላይ የሚወሰደው የእርምት እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል።
መቀሌ 70 እንደርታ ለኢትዮጵያ ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ አለፈ
Apr 22, 2026 111
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ ቦዲቲ ከተማን 3 ለ 2 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፍጹም ዓለሙ፣ ፕሪንስ ኦፎሪ እና ቦና ዓሊ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሙሉቀን ተስፋዬ እና ቴዎድሮስ በለጠ ለቦዲቲ ከተማ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ መቀሌ 70 እንደርታ ግማሽ ፍጻሜ የገባ የመጀመሪያ ቡድን ሆኗል። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር እስከ ሚያዚያ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
በክልሉ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት በትምህርት ቤቶች ውስጥ ቅንጅታዊ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Apr 22, 2026 72
ጅማ ፤ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ከመማር ማስተማር ሥራው ጎን ለጎን ብቁ እና ተወዳዳሪ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት በትምህርት ቤቶች ውስጥ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን የማጠናከር ሥራ በቅንጅት እየተከናወነ መሆኑ ተገለጸ። የጅማ ዞን ትምህርት ቤቶች ስፖርታዊ ውድድር በጅማ ከተማ የተጀመረ ሲሆን፣ በውድድሩ ላይ ከዞኑ የተለያዩ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ ከ530 በላይ ተማሪዎች ይሳተፋሉ። ውድድሩ ለሚቀጥሉት 10 ቀናት እንደሚቆይም ተገልጿል። በመክፈቻ ፕሮግራሙ ላይ የታደሙት የኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ካሳሁን ገላና (ዶ/ር)፣ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት የሚረጋገጠው በትምህርት እና በቴክኖሎጂ ነው ብለዋል። ጠንካራ የትምህርት ተቋማትን መገንባት የሚቻለው በዕውቀትም ሆነ በአካል የጎለበቱ ተማሪዎችን ማፍራት ሲቻል መሆኑን ጠቅሰው፣ ይህንን ግብ ለማሳካትም ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ የመማር ማስተማር ሥራውን ውጤታማ ከማድረግ ጎን ለጎን ትምህርት ቤቶች ተተኪ ስፖርተኞች ማፍሪያ ስፍራ እንዲሆኑ ትኩረት ተደርጓል ነው ያሉት። የጅማ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ቲጃኒ ናስር በበኩላቸው፣በዞኑ የስፖርት ማዘውተሪያዎችን የማስፋፋት፣ ምቹ ሁኔታዎችን የመፍጠርና የስፖርት ትጥቆችን የማሟላት ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። የጅማ ዞን ትምህርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሚፍታ አብዱልቃድር እና የዞኑ ወጣቶችና ስፖርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነጉማ መኮንን፣ በዞኑ ሁሉም ትምህርት ቤቶች ስፖርትን የማጠናከር ሥራ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ ቀደም ከትምህርት ቤቶች የወጡ ወጣቶች በዓለም አቀፍ መድረክ ኢትዮጵያን ማስጠራት መቻላቸውን አስታውሰው፣ ነገ አገርን የሚያስጠሩ ስፖርተኞችን ለማፍራት የትምህርት ተቋማትን የመደገፍና የማበረታታት ሥራው ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በውድድሩ ላይ ለመሳተፍ ከሲጊሞ ወረዳ የመጣው ተማሪ መሀመድ ከሊፋ እና ከሰቃ ጨቆርሳ የመጣችው ተማሪ ተንዚላ ዛኪር በሰጡት አስተያየት፤ በትምህርት ቤቶቻቸው ውስጥ እንደ ፍላጎታቸውና ተሰጥኦዋቸው በሳምንት ሦስት ቀን ልምምድ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል። አስፈላጊው ስፖርታዊ ትጥቅና የመለማመጃ ስፍራም እንደተመቻቸላቸው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ዛሬ ይጀመራል
Apr 22, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ ዛሬ በቦዲቲ ከተማ እና መቀሌ 70 እንደርታ መካከል ይደረጋል። ጨዋታው ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል። በጥሎ ማለፉ ቦዲቲ ከተማ ባህር ዳር ከተማን፣ መቀሌ 70 እንደርታ ኢትዮጵያ ቡናን አሸንፈዋል። ቦዲቲ ከተማ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ምድብ ለ በ21 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሚገኘው መቀሌ 70 እንደርታ በ29 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የዛሬው ጨዋታ አሸናፊ ቡድን የመጀመሪያው የግማሽ ፍጻሜ አላፊ ይሆናል። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች እስከ ሚያዝያ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያሉ። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሚያሸንፍ ቡድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል። ውድድሩ ከ1937 ዓ.ም አንስቶ እየተካሄደ ይገኛል።
ማንችስተር ሲቲ የሊጉ መሪ ለመሆን ከበርንሌይ ጋር ይጫወታል
Apr 22, 2026 235
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት አራት ሰዓት ላይ በርንሌይ ከማንችስተር ሲቲ በተርፍ ሙር ስታዲየም ይጫወታሉ። በርንሌይ በ20 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው ማንችስተር ሲቲ በ67 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለሜዳው በርንሌይ ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት ያለውን ጭላንጭል ተስፋ ለማለምለም ያግዘዋል። ማንችስተር ሲቲ ካሸነፈ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው የሊጉን መሪነት ከአርሰናል ይረከባል። ማንችስተር ሲቲ በሳምንቱ መጨረሻ ከሊድስ ዩናይትድ ጋር በሚያደርገው የኤፍኤ ካፕ ግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ምክንያት ፣ የ34ኛ ሳምንት ጨዋታውን ዛሬ አስቀድሞ ያደርጋል። በሌላኛው መርሐ ግብር ቦርንማውዝ ከሊድስ ዩናይትድ ምሽት አራት ሰዓት ላይ በቫይታሊቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቦርንማውዝ በ48 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት 13 የሊግ ጨዋታዎች አልተሸነፈም። ቦርንማውዝ ካሸነፈ ባለመሸነፍ ጉዞው ይቀጥላል። በአውሮፓ መድረክ የመሳተፍ እድሉን ያሰፋል። ሊድስ ዩናይትድ በ39 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ካሸነፈ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን የሚያስመዘግብ ሲሆን ከወራጅ ቀጠና የሚርቅበትንም እድል ያገኛል።
ቼልሲ በብራይተን ተሸነፈ
Apr 22, 2026 173
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 34ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ብራይተን ቼልሲን 3 ለ 0 አሸንፏል። በአሜክስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፌርዲ ካዲዮግሉ፣ ጃክ ሂንሼልውድ እና ዳኒ ዌልቤክ ለብራይተን የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ከፍተኛ ብልጫ የነበረው ብራይተን ተጨማሪ ጎሎችን ማስቆጠር የሚችልባቸውን እድሎች አምክኗል። ደካማ እንቅስቃሴ ያደረገው ቼልሲ በጨዋታው ኢላማ የጠበቀ ሙከራ አላደረገም። በሊጉ 13ኛ ድሉን ያስመዘገበው ብራይተን በ50 ነጥብ ደረጃውን ከዘጠነኛ ወደ ስድስተኛ ከፍ አድርጓል። በአውሮፓ መድረክ ለመሳተፍ እያደረገ ባለው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቼልሲ በ48 ነጥብ ከነበረበት ስድስተኛ ደረጃ ወደ ዘጠነኛ ዝቅ ብሏል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች የተሸነፈው ቼልሲ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የመሳተፍ እድሉ ይበልጥ ተመናምኗል።
ሁለተኛው ብሔራዊ የቦክስ ክለቦች ሻምፒዮና ተጀመረ
Apr 21, 2026 220
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የ2018 ዓ.ም ሁለተኛው ብሔራዊ የቦክስ ክለቦች ውድድር ዛሬ በራስ ኃይሉ የትምህርት እና ስፖርት ስልጠና ማዕከል ዛሬ መካሄድ ተጀምሯል። በውድድሩ በሁለቱም ጾታዎች ከ12 ክለቦች የተወጣጡ 120 ተወዳዳሪዎች ይሳተፋሉ። አዲስ አበባ ፖሊስ፣ ኦሜድላ፣ ፌዴራል ማረሚያ ቤቶች፣ ዩናይትድ ስዊት፣ የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ፣ ወወክማ፣ ኤቲ፣ ተወልደ፣ ሰሜን ሸዋ፣ ደብረ ብርሃን፣ ድሬዳዋ ከተማ እና ሀድያ ተሳታፊ ክለቦች ናቸው። በወንዶች ከ48 እስከ 86 ኪሎ ግራም፤ በሴቶች ከ48 እስከ 60 ኪሎ ግራም ውድድሩ የሚካሄድባቸው የክብደት ዘርፎች ናቸው። የኢትዮጵያ ቦክስ ፌዴሬሽን የጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ስንታየሁ ተስፋዬ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የውድድሩ አላማ በሁለቱም ጾታዎች ለኢትዮጵያ ቦክስ ብሔራዊ ቡድን የሚሆኑ ተወዳዳሪዎችን መምረጥ ነው። ውድድሩ በዓመት አራት ጊዜ የሚካሄድ በመሆኑ ለቦክስ ክለቦች የውድድር አማራጭን እንደሚያሰፋ ተናግረዋል። የዘንድሮው የመጀመሪያ ውድድር በህዳር ወር 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ትንሿ ስታዲየም መካሄዱን አስታውሰዋል። ሶስተኛው ውድድር በግንቦት ወር 2018 ዓ.ም በአርባምንጭ ከተማ፣ አራተኛው በሰኔ ወር አጋማሽ በአዲስ አበባ እንደሚካሄድም ነው የጽህፈት ኃላፊው የጠቆሙት። በከተሞቹ የሚካሄዱት ውድድሮች አጠቃላይ ውጤት ተደምሮ በሁለቱም ጾታዎች አጠቃላይ አሸናፊ ክለቦች እንደሚለዩም አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ቦክስ ፌዴሬሽን የውድድር እና ስልጠና ከፍተኛ ባለሙያ ኢንስትራክተር ካሳሁን ምንተስኖት በበኩላቸው፤ ውድድሩ ለታዳጊ ስፖርተኞች የውድድር ተሳትፎ በር የሚከፍት እና ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት እንደሚያግዝ አመልክተዋል። በውድድሮቹ ላይ የሚገኙ ተወዳዳሪዎች ኢትዮጵያን በመወከል የሀገርን ስም የማስጠራት እድል እንደሚያገኙም ተናግረዋል። በቀጣይ በግል ተቋማት መካከል የሚደረግ የቦክስ ውድድር ለማዘጋጀት መታቀዱንና ይህም የውድድር አማራጮችን ለማስፋት እንደሚያስችል ነው ያብራሩት። የቦክስ ፌዴሬሽን ከክልሎች እና ከክለቦች ጋር በመተባበር በታዳጊዎች ስፖርት ልማት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸው የቁሳቁስ ድጋፍ እና ስልጠናን ጨምሮ የተለያዩ የአቅም ግንባታ ድጋፎችን እያደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቦክስ ኮንፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ እያሱ ወሰን አማካኝነት የአህጉሪቷን የቦክስ ልማት ለማሳደግ እየሰራች እንደምትገኝ አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በፕሬዝዳንትነቷ የቦክስ ስፖርት ስራዋን ለአፍሪካ እና ለተቀረው ዓለም የማሳየት እድል ማግኘቷንም ነው ያነሱት። በዛሬው የውድድር መክፈቻ 21 የማጣሪያ ውድድሮች ተካሂደዋል። የ2018 ዓ.ም ሁለተኛው ብሔራዊ የቦክስ ክለቦች ውድድር እስከ ሚያዝያ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። አዲስ አበባ ፖሊስ በ2018 ዓ.ም የመጀመሪያ ብሔራዊ የቦክስ ክለቦች ውድድር በሁለቱም ጾታዎች በካታጎሪ ኤ የውድድር አይነት አጠቃላይ አሸናፊ እንደነበር የሚታወስ ነው። በወቅቱ ፌደራል ማረሚያ ቤቶች በካታጎሪ ቢ አጠቃላይ ማሸነፉ አይዘነጋም።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ድል ቀንቶታል
Apr 21, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ28ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስ አዳማ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፍጹም ጥላሁን በ71ኛው ደቂቃ ግቧን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን ያስመዘገበው ቅዱስ ጊዮርጊስ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ35 ነጥብ ደረጃውን ከ14ኛ ወደ 10ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ ከነበረበት 13ኛ ደረጃ ወደ 14ኛ ዝቅ ብሏል። አዳማ ከተማ ባለፉት ስምንት የሊጉ ጨዋታዎች ከድል በመራቅ የውጤት ማጣት ቀውስ ውስጥ ይገኛል። ጨዋታውን ተከትሎ የ28ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ተጠናቋል። ፕሪሚየር ሊጉ በኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ምክንያት የሚቋረጥ ሲሆን፤ በ29ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሚያዝያ 21 ቀን 2018 ዓ.ም ወደ ውድድር ይመለሳል።
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 34ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል
Apr 21, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛሬ በብራይተን እና ቼልሲ መካከል ይደረጋል። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በአሜክስ ስታዲየም ይካሄዳል። ብራይተን በ47 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ቼልሲ በ48 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ33ኛው ሳምንት ከቶተንሃም ሆትስፐርስ ጋር አንድ አቻ የተለያየው ብራይተን ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ብራይተን ካሸነፈ ተጋጣሚውን ቼልሲ በመብለጥ ስድስተኛ ደረጃን ይይዛል። የምዕራብ ለንደኑ ቼልሲ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ተሸንፏል። ሽንፈቶቹ ቡድኑ ሻምፒዮንስ ሊግ የመግባት ተሳትፎውን ይበልጥ እንዲጠብ አድርገዋል። ቼልሲ በአውሮፓ መድረክ የመሳተፍ ህልሙን እውን ለማድረግ ጨዋታውን የግድ ማሸነፍ ይጠበቅበታል። በኤፍኤ ካፕ ግማሽ ፍጻሜ በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት የሚጫወቱት ማንችስተር ሲቲ፣ ቼልሲ እና ሊድስ ዩናይትድ የ34ኛ ሳምንት ጨዋታቸውን አስቀድመው ያደርጋሉ። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 34ኛ ሳምንት እስከ ሚያዚያ 19 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአዳማ ከተማ ጋር ይጫወታል
Apr 21, 2026 121
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአዳማ ከተማ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቅዱስ ጊዮርጊስ በውድድር ዓመቱ 26 ጨዋታዎችን አድርጎ በስምንቱ ሲያሸንፍ በ10ሩ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ስምንት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። በ26ቱ ጨዋታዎች 22 ግቦችን ሲያስቆጥር 24 ጎሎችን አስተናግዷል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ32 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ካከናወናቸው 27 ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ያሸነፈው አዳማ ከተማ በበኩሉ ስምንት ጊዜ ተሸንፎ በ12 ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። ባደረጋቸው ጨዋታዎችም 24 ግቦችን ሲያስቆጥር 28 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ27ኛ ሳምንት ከአርባምንጭ ከተማ ጋር ሁለት አቻ የተለያየው ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ባለፉት ሰባት የሊጉ ጨዋታዎች ከድል የራቀው አዳማ ከተማ ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል።
ክሪስታል ፓላስ እና ዌስትሃም ዩናይትድ ነጥብ ተጋሩ
Apr 21, 2026 114
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ክሪስታል ፓላስ እና ዌስትሃም ዩናይትድ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ትናንት ማምሻውን በሰልኸርስት ፓርክ በተካሄደው ጨዋታ ዌስትሃም ከተጋጣሚው የተሻሉ የግብ እድሎችን ቢፈጥርም ወደ ግብ መቀየር አልቻለም። ባለሜዳው ክሪስታል ፓላስ አንጻራዊ የኳስ ቁጥጥር ብልጫውን ወደ ጎል እድሎች በሚገባ መቀየር አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ ክሪስታል ፓላስ በ43 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ33 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ከመውረድ ስጋቱ አልተላቀቀም። የአቻ ውጤቱን ተከትሎ በ17 ነጥብ 20ኛ ደረጃን የያዘው ዎልቭስ አምስት ጨዋታዎች እየቀሩት ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱ ተረጋግጧል። የ33ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ፍጻሜያቸውን አግኝተዋል። የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል።
ወላይታ ድቻ ድል ሲቀናው ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ኢትዮጵያ መድን ነጥብ ተጋርተዋል
Apr 20, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ጨዋታዎች መካሄዳቸውን ቀጥለዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው መርሐ ግብር ወላይታ ድቻ ምድረ ገነት ሽሬን 1 ለ 0 ረትቷል። ያሬድ ዳርዛ በ64ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉን ያስመዘገበው ወላይታ ድቻ በ34 ነጥብ ደረጃውን ከ16ኛ ወደ 10ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ምድረ ገነት ሽሬ በ29 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች ከድል በመራቅ የውጤት ማጣት ቀውስ ውስጥ ይገኛል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ ተለያይተዋል። በዛብህ መለዮ በ67ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ግብ ኢትዮ ኤሌክትሪክ መሪ ሆኗል። ይሁንና አማኑኤል ኤርቦ በ84ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል ለኢትዮጵያ መድን አንድ ነጥብ አስገኝታለች። ሀሰን ሁሴን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ፣ አብዱል ጋንዩ ከኢትዮጵያ መድን በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥተዋል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አምስተኛ ከፍ አድርጓል። ኢትዮጵያ መድን በ31 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን ባለፉት አራት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። በተመሳሳይ ዛሬ በተደረገ የ28ኛ ሳምንት ጨዋታ ሸገር ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል።
ሸገር ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Apr 20, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ሸገር ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቢንያም ፍቅሩ እና ቡልቻ ሹራ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ከሶስት የሊግ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሸገር ከተማ በ35 ነጥብ ደረጃውን ከ12ኛ ወደ 9ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ያሸነፋቸው ጨዋታዎች ብዛት ሰባት ደርሰዋል። በአንጻሩ በሊጉ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ባህር ዳር ከተማ በ36 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም።
በሐረሪ ክልል ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የሚያስችሉ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ ነው
Apr 20, 2026 189
ሐረር ፤ሚያዚያ 12/2018 (ኢዜአ) ፡-በሐረሪ ክልል በስፖርት ዘርፍ በሚከናወኑ ስራዎች ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ምቹ ሁኔታ እየተፈጠሩ መሆኑን የስፖርት ቤተሰቦች ገለጹ። በክልሉ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ልማትና የፕሮጀክት ስልጠናዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑ ተመላክቷል ። በክልሉ የሐረር ጀጎል እግር ኳስ ክለብ አሰልጣኝ አክረም መሀመድ ለኢዜአ እንደገለጸው በክልሉ ከዚህ ቀደም ተተኪ ስፖርተኞችን የማፍራትና የድጋፍና እገዛ ተግባራት ትኩረት ተነፍጎት ቆይቷል። በአሁኑ ወቅት ህፃናትና ታዳጊዎች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ጠቁሞ ለዘርፉ ስልጠና የተሰጠው ትኩረት አሰልጣኞችንም እያበረታታ መሆኑን አመልክቷል ። በክልሉ እየተከናወኑ ያሉ የስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታና የድጋፍ ስራዎች ተሰጥኦ ያላቸው ታዳጊዎችን ወደ ስፖርቱ ለመምጣት ምቹ ሁኔታ እየፈጠሩ ነው ያሉት ደግሞ የታዳጊ ፕሮጀክት እግር ኳስ አሰልጣኝ ኢንስፔክተር ፈይሰል መሀመድ ናቸው። በተለይ ቀደም ሲል እንደ ችግር ሆኖ ጥያቄ ሲቀርብባቸው የነበሩ ተቀራርቦ የመስራት ተግዳሮቶችን ለመፍታት በተከናወኑ ተግባራት ውጤት እየተገኘ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህም የቅንጅት ስራዎች እየጎለበቱ በመሆኑ ተተኪ ስፖርተኞችን የማፍራት ተግባራትን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ አመላክተዋል። የታዳጊ ፕሮጀክት ሰልጣኝ የሆነው ማስተዋል ታጠቅ በበኩሉ “በከተማው ከኮሪደር ልማት ጋር በማስተሳሰር በየአካባቢው የተከናወኑ የስፖርት ማዘወተሪያ ስፍራዎች ተሰጧችንን ለማውጣት እድል እየፈጠሩልን ነው ብሏል። በተለይ በታዳጊዎች ፕሮጀክት ታቅፈን የሚሰጠን ስልጠና ወደፊት ታላላቅ ክለቦች ላይ መሳተፍ የሚያስችለን ክህሎት እየወሰድን እንገኛለን ፤ እኛም ደግሞ በተገቢው መንገድ እየሰራን እንገኛለን ሲል ገልጿል። በክልሉ ለታዳጊ ፕሮጀክት ስልጠና እየተደረገ የሚገኘው ድጋፍና በየአካባቢው የስፖርት ማዘውተርያ ስፍራ ግንባታ ተስፋ የሚሰጡ ስራዎች ሆነው አግኝተናቸዋል ያለው ሌላው የታዳጊ ፕሮጀክት ሰልጣኝ አብረሃም አሸናፊ ነው። እኛም የነገዋ ኢትዮጵያ የምትጠብቅብንን አሸናፊነት ለማምጣት ከወዲሁ ተግተን እየሰራን እንገኛለን ብሏል የሐረሪ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙራድ አብዲ በበኩላቸው በክልሉ የስፖርት ማዘውተሪያ ስራዎችን የማልማትና ፋሲሊቲዎችን በማሟላት ተተኪ ስፖርተኞችን የማፍራት ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በዚህም የክልሉ መንግስት ቀደም ሲል የነበሩ የማዘውተርያ ስፍራዎችን የማዘመን እንዲሁም በየወረዳው አንድ የስፖርት ማዘውተርያ ስፍራ የመገንባት ስራ በእቅድ ይዞ እያከናወነ ይገኛል ሲሉ ተናግረዋል። እግር ኳስን ጨምሮ በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ክልሉን ብሎም ሀገርን ወክለው በዓለም አቀፍ መድረክ የሚወዳደሩ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ የታዳጊ ፕሮጀክት ስልጠናዎች አዲስ ፎርማት ተቀርጾላቸው ስልጠና እየተሰጠ መሆኑን አመልክተዋል።
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን 29ኛው ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ መካሄድ ጀመረ
Apr 20, 2026 108
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን 29ኛው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ዛሬ በአዲስ አበባ ማካሄድ ጀምሯል። እስከ ነገ ድረስ በሚቆየው በዚህ ጉባኤ ላይ የ2017 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ውይይት ተደርጎበት ጸድቋል። ጉባኤው የውጭ ኦዲተርን የመሰየም እንዲሁም የ2017 በጀት ዓመት የውጭ ኦዲት ሪፖርትን በማዳመጥ ተወያይቶ የማጽደቅ አጀንዳዎችን ይዟል። በተጨማሪም የ2018 በጀት ዓመት የሥራ ዕቅድና በጀት ላይ በመምከር ውሳኔ የሚያሳልፍ ይሆናል። ሌላው በጉባኤው የሚዳሰሰው ጉዳይ ተቋማዊ አሰራር (ሪፎርም) ሰነድ እና የሰው ኃይል መዋቅራዊ ጥናትን ተመልክቶ ማጽደቅ ሲሆን፣ የተሻሻለውን የፌዴሬሽኑ መተዳደሪያ ደንብም መርምሮ ያጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል። ጉባኤው የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድን እንዲሁም የተሻሻለውን የፌዴሬሽኑ የግዥ፣ ፋይናንስና ንብረት አስተዳደር መመሪያን በአጀንዳነት በመያዝ ውይይት በማድረግ እንደሚያጸድቅ የፌዴሬሽኑ መረጃ ያመለክታል።
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
Apr 20, 2026 130
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ ግብር ዛሬ በክሪስታል ፓላስ እና ዌስትሃም ዩናይትድ መካከል ይካሄዳል። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ላይ በሰልኸረስት ፓርክ ስታዲየም ይካሄዳል። ክሪስታል ፓላስ በ42 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ32 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሲገናኙ የአሁኑ ለ35ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 34 ጨዋታዎች ክሪስታል ፓላስ በ13ቱ ሲያሸንፍ ዌስትሃም በ11ዱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ 10 ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርተዋል። በ34ቱ ጨዋታዎች ክሪስታል ፓላስ 52 ግቦችን ሲያስቆጥር፣ ዌስትሃም ዩናይትድ 50 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቡድኖቹ ባለፉት አምስት የሊግ ግንኙነታቸው ፓላስ ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ዌስትሃም አንድ ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት በአምስተኛ ሳምንት በለንደን ስታዲየም ተገናኝተው ክሪስታል ፓላስ 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በ32ኛ ሳምንት ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 1 ያሸነፈው ክሪስታል ፓላስ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። በተመሳሳይ በ32ኛ ሳምንት ዎልቭስን 4 ለ 0 የረታው ዌስትሃም ዩናይትድ ከወራጅ ቀጠናው ለመራቅ ሶስት ነጥብ ማግኘት ወሳኝ ነው። ሁለቱ የለንደን ክለቦች በጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ያሳያሉ ተብሎ ይጠበቃል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ውሎ
Apr 20, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይከናወናሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከኢትዮጵያ መድን በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ41 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ መድን በ30 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ27ኛ ሳምንት አዳማ ከተማን 1 ለ 0 ያሸነፈው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በድል ጉዞው ለመቀጠል ይጫወታል። የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። መድን ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት የሚያስችለውን ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባህር ዳር ከተማ በ36 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ሸገር ከተማ በ32 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ27ኛ ሳምንት ከኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ የተለያየው ባህር ዳር ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በበርካታ ጨዋታዎች (15 ጊዜ) አቻ የወጣ ቡድን ነው። ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ያላሸነፈው አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና አካባቢ እንዲርቅ ያስችለዋል። ምድረ ገነት ሽሬ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 10 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረ ገነት ሽሬ በ29 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ወላይታ ድቻ በ31 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ምድረ ገነት ሽሬ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ትግል ሶስት ነጥብ ማግኘት ግድ ይለዋል። በ27ኛ ሳምንት በፋሲል ከነማ 1 ለ 0 የተሸነፈው ወላይታ ድቻ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታል።
ሲዳማ ቡና የሊጉን መሪነት ያጠናከረበት ወሳኝ ድል አስመዘገበ
Apr 19, 2026 569
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ28ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አቤል ያለው ግቦቹን አስቆጥሯል። በሊጉ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በ54 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ መቻል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ 10 ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ32 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ 14 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን አጠናክሯል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር መቻል እና ሃዋሳ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። መቻል በ44 ነጥብ ሁለተኛ፣ ሃዋሳ ከተማ በ43 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። ነገሌ አርሲ ከሀድያ ሆሳዕና አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኪቲካ ጅማ ለነገሌ አርሲ፣ ተመስገን ብርሃኑ ለሀድያ ሆሳዕና ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ነገሌ አርሲ በ44 ነጥብ ሶስተኛ፣ ሀድያ ሆሳዕና በ34 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ዛሬ በአዲስ አበባ ስታዲየም አስቀድሞ የተካሄደው የኢትዮጵያ ቡና እና አርባምንጭ ከተማ ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። ቢንያም ጌታቸው ለኢትዮጵያ ቡና፣ ይድነቃቸው ያሲን ለአርባምንጭ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ኢትዮጵያ ቡና በ38 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ24 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ባየር ሙኒክ የቡንድስሊጋ ዋንጫን ለ35ኛ ጊዜ ማንሳቱን አረጋገጠ
Apr 19, 2026 331
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- በጀርመን ቡንድስሊጋ 30ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ባየር ሙኒክ ስቱትጋርትን 4 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሃሪ ኬን፣ ኒኮላስ ጃክሰን፣ አልፎንሶ ዴቪስ እና ራፋኤል ጉሬሮ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ቼማ አንድሬስ እና ክሪስ ፉህሪች ለስቱትጋርት ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሊጉ 25ኛ ድሉን ያስመዘገበው ባየር ሙኒክ አራት ጨዋታ እየቀረው የቡንደስሊጋ ዋንጫን ማንሳቱን አረጋግጧል። ለ35ኛ ጊዜ ጊዜ ቡንድስሊጋውን በማሸነፍ የጀርመን የበላይነቱን አስመስክሯል። ሙኒክ ካለፉት 15 የቡንድስሊጋ ዋንጫዎች 14ቱን አንስቷል።