ቀጥታ፡
ስፖርት
ማንችስተር ዩናይትድ ኖቲንግሃም ፎረስትን አሸነፈ
May 17, 2026 98
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፡- በ37ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ኖቲንግሃም ፎረስትን በኦልድትራፎድ ያስተናገደው ማንችስተር ዩናይትድ 3 ለ 2 ረትቷል። የማንችስተር ዩናይትድን ግቦች፤ በ5ኛው ደቂቃ ሉክ ሾው፣ ማቲውስ ኩንያ በ54ኛው ደቂቃ እንዲሁም ምቤሞ በ75ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የኖቲንግሃም ፎረስትን ግቦች ደግሞ፤ በ52ኛው ደቂቃ ሞራቶ በ77ኛው ደቂቃ ጊብስ ዋይት አስቆጥረዋል። የጨዋታውን ውጤት ተከትሎም ማንችስተር ዩናይትድ በ68 ነጥብ ባለበት 3ኛ ደረጃ ላይ ሲሆን፤ ኖቲንግሃም ፎረስት በ43 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ፖርቹጋላዊው አማካይ ብሩኖ ፈርናንዴዝ በውድድር ዓመቱ 20 ለግብ የሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል፤ በቴሪ ሄንሪ እና ኬቨን ዴብሮይን ተይዞ የነበረውን በአንድ ዓመት ብዙ ጎል አመቻችቶ የማቀበል ክብረ ወሰን ተጋርቷል። የዕለቱ የጨዋታ መርሐ-ግብሮች ሲቀጥሉ፤ በተመሳሳይ 11 ሠዓት ላይ ብሬንትፎርድ ከፓላስ፣ ሊድስ ከብራይተን፣ ዎልቭስ ከፉልሃም፣ ኤቨርተን ከሰንደርላንድ የሚጫወቱ ይሆናል። በሌላ በኩል ኒውካስትል ከዌስትሃም ምሽት 1 ሠዓት ከ30 ላይ እንደሚጫወቱ የወጣው መርሐ-ግብር ያስረዳል፡፡
ዋንጫውን ማን ያነሳል? ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ?
May 17, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል። ጨዋታው ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባደረጋቸው 25 ጨዋታዎች 21 ድሎችን ሲቀዳጅ የተሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 71 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ስምንት ጎሎችን ብቻ አስተናግዷል። ንግድ ባንክ በ66 ነጥብ ሊጉን እየመራ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ በርካታ ግቦችን ያስቆጠረ እና አነስተኛ የጎል መጠን ያስተናገደ ቡድን ነው። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በውድድር ዘመኑ 25 ጨዋታዎችን አከናውኖ በ21ዱ ሲያሸንፍ በአንድ ጨዋታ ብቻ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። በ24ቱ ጨዋታዎች ላይ 52 ግቦችን ሲያስቆጥር 12 ጎሎችን ተቆጥረውበታል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በተመሳሳይ 66 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 63 እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ 41 የግብ ክፍያ አላቸው። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ ለስድስተኛ ተከታታይ የውድድር ዓመት ዋንጫውን ያነሳል። በአጠቃላይ ለዘጠነኛ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ይሆናል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሊጉን ለማሸነፍ የግድ ጨዋታውን ማሸነፍ ይኖርበታል። ቡድኑ ካሸነፈ ለመጀመሪያ ጊዜ የፕሪሚየር ሊጉን ዋንጫ ያነሳል። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በ24 ግቦች ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የምትመራው የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን፣ በ20 ግቦች የምትከተለው የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ በጨዋታው ትኩረት ያገኙ ተጫዋቾች ናቸው። ሁለቱ ቡድኖች በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ተገናኝተው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን በማህሌት ምትኩ ጎል 1 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር መቻል ከአዲስ አበባ ከተማ ከረፋዱ አምስት ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቻል በ55 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ መውረዱ የተረጋገጠው አዲስ አበባ ከተማ በ15 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የመጨረሻ ሳምንት የሆነው የ26ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከ25ኛ ሳምንት በፊት አስቀድሞ ተደርጓል። የመርሐ ግብሩ ቅያሬ ከዋንጫ ተፎካካሪዎቹ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር የተገናኘ መሆኑ ተገልጿል። የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ፍጻሜውን ያገኛል።
ማንችስተር ዩናይትድ ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር ይጫወታል
May 17, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት ዛሬ ስድስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ 8 ሰዓት ከ30 ላይ ማንችስተር ዩናይትድ ኖቲንግሃም ፎረስትን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም ያስተናግዳል። የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን ያረጋገጠው ማንችስተር ዩናይትድ በ65 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኖቲንግሃም ፎረስት በ43 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ዩናይትድ ካሸነፈ በሊጉ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁን ያረጋግጣል። ጨዋታው ጊዜያዊው አሰልጣኝ ማይክል ካሪክ በክለቡ በቋሚነት የሚቀጥልበት የሁለት ዓመት ውል በተፈራረመ ማግስት የሚደረግ መሆኑ ትኩረትን ስቧል። በፕሪሚየር ሊጉ መቆየቱን ያረጋገጠው ኖቲንግሃም ፎረስት ከ36ኛ ሳምንት የአቻ ውጤት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል።     በሌላኛው መርሐ ግብር ኒውካስትል ዩናይትድ ከዌስትሃም ዩናይትድ ምሽት 1 ሰዓት ከ30 በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኒውካስትል ዩናይትድ በ46 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ36 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የመውረድ አጣብቂኝ ውስጥ የገባው ዌስትሃም ዩናይት ካሸነፈ በጊዜያዊነት ከወራጅነት ቀጠና በመውጣት ቶተንሃም ሆትስፐርስ ላይ ጫና ያሳድራል። በ36ኛ ሳምንት ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር አንድ አቻ የተለያየው ኒውካስትል ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። ብሬንትፎርድ ከክሪስታል ፓላስ፣ ሊድስ ዩናይትድ ከብራይተን፣ ዎልቭስ ከፉልሃም እና ኤቨርተን ከሰንደርላንድ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በአዘጋጇ ሞሮኮ ተሸነፈ
May 16, 2026 312
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አንድ መርሐ ግብር ሞሮኮ ኢትዮጵያን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ማምሻውን በመሐመድ ስድስተኛ ስፖርት አካዳሚ በተካሄደው ጨዋታ ዳዊት ካሳው በ24ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ኢትዮጵያ መሪ ሆናለች። ከእረፍት መልስ በ47ኛው ደቂቃ መሐመድ ሙስታሽ ሞሮኮን አቻ ያደረገችውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ ተብሎ ሲጠበቅ ኢምራን ታላይ በ91ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ሞሮኮን አሸናፊ አድርጓል። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በጨዋታው ጥሩ የማጥቃት እንቅስቃሴ ያደረገ ሲሆን ተጨማሪ ግቦችን ማስቆጠር የሚችልባቸውን እድሎች መጠቀም አልቻለም። ብሔራዊ ቡድኑ ውጤቱን ተከትሎ በአንድ ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በመጀመሪያ ጨዋታው ከግብጽ ጋር አቻ መውጣቱ ይታወቃል። አዘጋጇ ሞሮኮ በአራት ነጥብ ምድብ አንድን እየመራች ነው። ሞሮኮ የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ናት። ዛሬ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ግብጽ ቱኒዚያን በማሸነፍ በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በአሜሪካዊው ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው ብሔራዊ ቡድን የመጨረሻ የምድብ ጨዋታውን ማክሰኞ ግንቦት 11 ቀን 2018 ዓ.ም ከቱኒዚያ ጋር ያደርጋል። ቡድኑ በኳታር ለሚካሄደው የዓለም ዋንጫ የማለፍ ተስፋውን ለማለምለም ሶስት ነጥብ ማግኘት ግድ ይለዋል። ሞሮኮ ከግብጽ ሌላኛው የሚደረግ የመጨረሻ የምድብ ጨዋታ ነው።
ፋሲል ከነማ ወደ ድል ተመልሷል
May 16, 2026 235
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ፋሲል ከነማ አዳማ ከተማን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ታምራት ኢያሱ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ቃልኪዳን ዘላለም ቀሪዋን ጎል ለፋሲል ከነማ ከመረብ ላይ አሳርፏል። የፋሲል ከነማው አብዱልአዚዝ አማን በራሱ መረብ ላይ ያስቆጠረው ጎል ለአዳማ ከተማ ብቸኛ ግብ ሆኖ ተመዝግቧል። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ፋሲል ከነማ በ46 ነጥብ ደረጃውን ከስምንተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉም 11ኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ38 ነጥብ በበኩሉ ከነበረበት 15ኛ ደረጃ ወደ 16ኛ ዝቅ ብሏል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ የ32ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 ሲያሸንፍ ሃዋሳ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የጨዋታዎቹን መጠናቀቅ ተከትሎ 32ኛ ሳምንት ፍጻሜውን አግኝቷል። የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከግንቦት 11 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳል።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒርሲቲ ድል ሲቀናው ሃዋሳ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ አቻ ተለያይተዋል
May 16, 2026 158
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መካሄዱን ቀጥሏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። ጋናዊው ኮንኮኒ ሃፊዝ እና እንዳልካቸው ጥበቡ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አቤል ሀብታሙ የኢትዮ ኤሌክትሪክን ብቸኛ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ39 ነጥብ ደረጃውን ከ16ኛ ወደ 15ኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉም ዘጠነኛ ድሉን አሳክቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ45 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው መርሐ ግብር ሃዋሳ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ሃዋሳ ከተማ በ45 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ዘጠኝ የሊጉ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ በውጤት ማጣት ቀውስ ይገኛል። አርባምንጭ ከተማ በ29 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሲሆን ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም።
ኢትዮጵያ በ20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር በሁለቱም ጾታዎች የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 16, 2026 164
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛ የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ አምስተኛ ቀኑን ይዟል። በወንዶች 20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር አትሌት ምስጋናው ዋቁማ አሸንፏል። ውድድሩን በአንደኝነት በማጠናቀቅ በአፍሪካ ሻምፒዮና መድረክ በተከታታይ ለሁለተኛ ጊዜ በማሸነፍ ክብሩን አስጠብቋል። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት አብዱልሰላም አብዱልዋሂብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ የነሐስ ሜዳሊያ ለሀገሩ አስገኝቷል።   በሴቶች 20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር ደግሞ አትሌት ውብአለም ሽጉጤ በቀዳሚነት አጠናቃ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። በዚሁ ውድድር ላይ የተካፈሉት አትሌት ሕይወት አምባው አራተኛ እንዲሁም አትሌት ማሬ ቢተው ስምንተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድራቸውን አጠናቀዋል። ውጤቶቹን ተከትሎ ኢትዮጵያ ያገኘቻቸው የወርቅ ሜዳሊያዎች ብዛት አምስት ደርሰዋል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው አምስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና አምስት የነሐስ በድምሩ 11 ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። ሻምፒዮናው ነገ ይጠናቀቃል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
May 16, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ36 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ45 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ማግኘት ያልቻለው ወልዋሎ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና ስፍራ ፈቀቅ እንዲል ያደርገዋል። በ31ኛ ሳምንት ፋሲል ከነማን 3 ለ 1 የረታው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ካሸነፈ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ሃዋሳ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባለፉት ስምንት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ በ44 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ28 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ በ31ኛ ሳምንት በወላይታ ድቻ የ3 ለ 2 ሽንፈት አስተናግዷል። ሃዋሳ ከተማ ከድል ጋር ለመታረቅ፣ አርባምንጭ ከተማ ላለመውረድ በሚያደርገው ትግል ሶስት ነጥብ ለማግኘት የሚያደርጉት ፍልሚያ ትኩረትን ስቧል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ፋሲል ከነማ ከአዳማ ከተማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ፋሲል ከነማ በ43 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። አዳማ ከተማ በ38 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ድል ያልቀናው ፋሲል ከነማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። በ31ኛ ሳምንት ምድረ ገነት ሽሬን 4 ለ 0 በመርታት ከስምንት ጨዋታዎች በኋላ ሶስት ነጥብ ያገኘው አዳማ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን የሞሮኮ አቻውን ይገጥማል
May 16, 2026 119
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት የሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ አራተኛ ቀኑን ይዟል። በምድብ አንድ የሚገኘው የኢትዮጵያ ታዳጊ ብሔራዊ ቡድን ሁለተኛ ጨዋታውን ዛሬ ከአዘጋጇ ሞሮኮ ጋር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ ኮምፕሌክስ ያደርጋል። ብሔራዊ ቡድኑ በመጀመሪያ ጨዋታው ከግብጽ ጋር ያለ ግብ አቻ በመውጣት አንድ ነጥብ አግኝቷል። ቡድኑ በጨዋታው ላይ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ አድርጓል። አዘጋጇ ሞሮኮ በመጀመሪያ ጨዋታ ቱኒዚያን 3 ለ 0 በማሸነፍ ምድቡን እየመራች ነው። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመዋር ቡድን ከምድቡ ለማለፍ እና በኳታር ለሚደረገው ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ የማለፍ ህልሙን ለማሳካት ከዛሬው ጨዋታ ሶስት ነጥብ ማግኘት ይጠበቅበታል። የአጥቂ መስመሩ የሚፈጠሩ የግብ ዕድሎችን ወደ ውጤት የመቀየር አቅሙን ማሳደግ ይኖርበታል። ብሔራዊ ቡድኑ ከጨዋታው በፊት የመጨረሻ ልምምዱን በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ አካዳሚ ማድረጉንና ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በዚሁ ምድብ ከቀኑ 10 ሰአት ላይ ቱኒዚያ ከግብጽ በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ ኮምፕሌክስ ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊጉ የ25ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን መርሐ ግብር
May 16, 2026 141
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከጠዋቱ ሶስት ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ባለፉት ሰባት ጨዋታዎች ከድል የራቀው አዳማ ከተማ በ22 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በ25 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሁለቱም ቡድኖች ዓመቱን አሸናፊነት ለማጠናቀቅ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ሸገር ከተማ ከይርጋጨፌ ቡና ከረፋዱ አምስት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሸገር ከተማ በ47 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ይርጋጨፌ ቡና በ18 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ26ኛ ሳምንት በቦሌ ክፍለ ከተማ 2 ለ 0 የተሸነፈው ሸገር ከተማ ዓመቱን በድል ለመቋጨት ይፋለማል። ይርጋጨፌ ቡና ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል።
የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ማን ያነሳል? ቼልሲ ወይስ ማንችስተር ሲቲ?
May 16, 2026 148
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ ቼልሲ እና ማንችስተር ሲቲ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ለማንሳት ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታው ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ 90 ሺህ ተመልካች በሚያስተናግደው ዌምብሌይ ስታዲየም ይካሄዳል። ቼልሲ ሊድስ ዩናይትድን እንዲሁም ማንችስተር ሲቲ ሳውዝሃምተንን በማሸነፍ ለፍጻሜው ማለፋቸው የሚታወስ ነው። ሁለቱ ክለቦች በኤፍኤ ካፕ ታሪካቸው ለ10ኛ ጊዜ የሚገናኙ ሲሆን፣ ቀደም ባሉት ዘጠኝ ግንኙነቶች ማንችስተር ሲቲ ስድስት ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። በአንጻሩ ቼልሲ በቀሪዎቹ ሶስት ጨዋታዎች ድል ቀንቶታል። በዘጠኙ ጨዋታዎች ላይ ማንችስተር ሲቲ 16 ግቦችን ሲያስቆጥር ቼልሲ ዘጠኝ ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቡድኖቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተገናኙት እ.አ.አ በ1915 በሶስተኛ ዙር ላይ ሲሆን ቼልሲ 1 ለ 0 አሸንፏል። እ.አ.አ በ2024 ለመጨረሻ ጊዜ በተገናኙበት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ 1 ለ 0 በመርታት ለፍፃሜው አልፏል። ቼልሲ ለኤፍኤ ካፕ ፍጻሜ ሲያልፍ ይህ ለ17ኛ ጊዜው ነው። የምዕራብ ለንደኑ ክለብ እስከ አሁን ስምንት ጊዜ የዋንጫው ባለቤት መሆን ችሏል። ማንችስተር ሲቲ ለ14ኛ ጊዜ ለፍጻሜ የደረሰ ሲሆን፣ እስካሁን ባደረጋቸው የፍጻሜ ጨዋታዎች ሰባት ጊዜ ዋንጫውን አንስቷል። ሁለቱ ቡድኖች ታሪካዊውን ዋንጫ ለማንሳት የሚያደርጉት ፍልሚያ ፣ ብርቱ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ቼልሲ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ካነሳ ለዩሮፓ ሊግ ማለፉን ያረጋግጣል። የ40 ዓመቱ ዳረን ኢንግላንድ ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። 154 ዓመታትን ያስቆጠረው ኤፍኤ ካፕ የዓለማችን እጅግ አንጋፋው የእግር ኳስ ውድድርነው።
አስቶንቪላ ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ማለፉን አረጋገጠ
May 16, 2026 135
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት የመጀመሪያ መርሐ ግብር አስቶንቪላ ሊቨርፑልን 4 ለ 2 ረቷል። በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኦሊ ዋትኪንስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሞርጋን ሮጀርስ እና ጆን ማጊን ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።   ቨርጅል ቫን ዳይክ ለሊቨርፑል ጎሎቹን አስቆጥሯል። በሊቨርፑሉ አማካይ ዶምኒክ ስቦዝላይ በተሰራው ስህተት ኦሊ ዋትኪንስ ያስቆጠረው ጎል የጨዋታው ቁልፍ ክስተት ነበር። ሊቨርፑል በጨዋታው የሰራቸው ስህተቶች ዋጋ አስከፍሎታል። ጨዋታው አዝናኝ እንቅስቃሴ የተደረገበት ሲሆን አስቶንቪላ ግልጽ የግብ እድሎችን በተሻለ ሁኔታ ፈጥሯል። በሊጉ 18ኛ ድሉን ያስመዘገበው አስቶንቪላ በ62 ነጥብ አራተኛ ደረጃን በመያዝ አንድ ጨዋታ እየቀረው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን አረጋግጧል። በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሊቨርፑል በ59 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመሳተፍ በ38ኛ ሳምንት ብሬንትፎርድን ማሸነፍ ይጠበቅበታል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም