ቀጥታ፡
ስፖርት
ማንችስተር ሲቲ ከብራይተን ይጫወታል 
Jan 7, 2026 73
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 29/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ስምንት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ ማንችስተር ሲቲ ከብራይተን በኢትሃድ ስታዲየም ጨዋታውን ያደርጋል። ማንችስተር ሲቲ በ42 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ብራይተን በ28 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ነጥብ የጣለው ማንችስተር ሲቲ ማሸነፍ ከአርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት በጊዜያዊነት ወደ ሶስት ዝቅ ማድረግ ያስችለዋል። ብራይተን ካሸነፈ በሊጉ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። በሌሎች መርሃ ግብሮች በርንሌይ ከማንችስተር ዩናይትድ ምሽት 5 ሰዓት ከ15 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን ያሰናበተው ማንችስተር ዩናይትድ በጊዜያዊ አሰልጣኝ ዳረን ፍሌቸር እየተመራ ወደ ሜዳ ይገባል። በርንሌይ ባለፉት 10 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ክሪስታል ፓላስ ከአስቶንቪላ፣ ፉልሃም ከቼልሲ፣ ብሬንትፎርድ ከሰንደርላንድ፣ ቦርንማውዝ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ኤቨርተን ከዎልቭስ በተመሳሳይ ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ። ኒውካስትል ዩናይትድ ከሊድስ ዩናይትድ ምሽት 5 ሰዓት ከ15 ላይ በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ባርሴሎና ከአትሌቲኮ ቢልባኦ ለስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ፍጻሜ ለማለፍ ይጫወታሉ
Jan 7, 2026 69
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 29/2018 (ኢዜአ)፦ የስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ የግማሽ የፍጻሜ መርሃ ግብር ዛሬ እና ነገ በሳዑዲ አረቢያ ይካሄዳል። ምሽት አራት ሰዓት ባርሴሎና ከአትሌቲኮ ቢልባኦ ጋር በኪንግ አብደላ ስፖርትስ ሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባርሴሎና 15 ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ የክብረ ወሰኑ ባለቤት ነው። አትሌቲኮ ቢልባኦ ሶስት ጊዜ ዋንጫውን አንስቷል። ሁለቱ ክለቦች በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለዘጠነኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ስምንት ጨዋታዎች ባርሴሎና አራት ጊዜ ሲያሸንፍ አትሌቲኮ ቢልባኦ ሶስት ጊዜ ድል ቀንቶታል። አንድ ጊዜ አቻ ወጥተዋል። ከስምንቱ ጨዋታዎች ስድስቱ የፍጻሜው ጨዋታ ደርሶ መልስ በነበረበት ወቅት የተካሄዱ ናቸው። እ.አ.አ በ2025 በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በጅዳ ባደረጉት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ባርሴሎና በጋቪ እና ላሚን ያማል ግቦች 2 ለ 0 አሸንፏል። እ.አ.አ በ2021 በፍጻሜው ተገናኝተው አትሌቲኮ ቢልባኦ 3 ለ 2 አሸንፏል። በ2025/26 የስፔን ላሊጋ ባርሴሎና በ49 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። አትሌቲኮ ቢልባኦ በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። የዛሬው ጨዋታ አሸናፊ ክለብ በፍጻሜው ከአትሌቲኮ ማድሪድ እና ሪያል ማድሪድ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። የስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ የተጀመረው እ.አ.አ 1982 ነው። ውድድሩ እ.አ.አ 1982 እስከ 2019 የስፔን ላሊጋ እና የስፔን የኮፓ ዴል ሬይ (ጥሎ ማለፍ) ዋንጫ አሸናፊዎች የሚጫወቱበት ነበር። የስፔን እግር ኳስ ማህበር እ.አ.አ በ2020 ባደረገው ማስተካከያ የስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በስፔን ላሊጋ እና በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ በተመሳሳይ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን የያዙ ክለቦች እንዲሳተፉ ተደርጓል። ባርሴሎና የወቅቱ የላሊጋ እና የኮፓ ዴል ሬይ አሸናፊ ሲሆን ሪያል ማድሪድ በሁለቱም ውድድሮች ላይ ሁለተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። እንደዚህ አይነት ሁኔታ በሚገጥምበት ወቅት በሊጉ ሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃን ይዘው ያጠናቀቁ ክለቦች እንደሚሳተፉ የውድድር ደንቡ ያስቀምጣል። በዚሁ መሰረት አትሌቲኮ ማድሪድ እና አትሌቲኮ ቢልባኦ በዘንድሮው ውድድር ላይ ተሳታፊ ሆነዋል።
የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ለሩብ ፍጻሜ አለፈች
Jan 7, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ኮትዲቯር ቡርኪናፋሶን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በማራካሽ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታው አማድ ዲያሎ በ20ኛው፣ ያን ዲዮማንዴ በ32ኛው እና ባዙማና ቱሬ በ87ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አማድ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ ሶስት ከፍ አድርጓል። ተጫዋቹ ከጎሉ በተጨማሪ ለዲዮማንዴ ጎል ኳሱን አመቻችቶ አቀብሏል። የጨዋታው ኮከብ ሆኖም ተመርጧል። በጨዋታው ላይ ኮትዲቯር ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ድሉን ተከትሎ የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ሩብ ፍጻሜ የገባች የመጨረሻዋ ሀገር ሆናለች። በሩብ ፍጻሜው ከሰባት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ግብጽ ጋር የምታደረገው ጨዋታ ከወዲሁ የሚጠበቅ ነው። ዛሬ በተደረገ ሌላኛው የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር አልጄሪያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን 1 ለ 0 በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅላች። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ተጠናቋል። አዘጋጇ ሞሮኮ ከካሜሮን፣ ኮትዲቯር ከግብጽ ፣ ናይጄሪያ ከአልጄሪያ እና ማሊ ከሴኔጋል በሩብ ፍጻሜው ይጫወታሉ። የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ጥር 1 እና 2 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳሉ።
ኖቲንግሃም ፎረስት ዌስትሃም ዩናይትድን በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Jan 7, 2026 69
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኖቲንግሃም ፎረስት ዌስትሃም ዩናይትድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በለንደን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የኖቲንግሃም ፎረስት ተከላካይ ሙሪሎ በ13ኛው ደቂቃ በራሱ ላይ ያስቆጠረው ጎል ዌስትሃምን መሪ አድርጓል። ኒኮላስ ዶሚኒጌዝ በ55ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፈው ጎል ኖቲንግሃም ፎረስት አቻ ሆኗል። ሞርጋን ጊብስ-ዋይት በ89ኛው በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠረው ግብ ለፎረስት ወሳኝ ሶስት ነጥብ አስገኝቷል። የዌስትሃም ዩናይትዱ ክሪሴንሲዮ ሳመርቪል በ51ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ከጨዋታ ውጪ በመሆኑ ምክንያት ሊሻር ችሏል። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኖቲንግሃም ፎረስት በ21 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ዌስትሃም ዩናይትድ በ14 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሌ። ዌስትሃም ዩናይትድ ባለፉት 10 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ታህሳስ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል 
Jan 6, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛሬ በዌስትሃም ዩናይትድ እና ኖቲንግሃም ፎረስት መካከል ዛሬ ይደረጋል። ጨዋታው ምሽት አምስት ላይ በለንደን ስታዲየም ይካሄዳል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ14 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኖቲንግሃም ፎረስት በ17 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ከቡርኪናፋሶ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው ባለሜዳው ዌስትሃም ዩናይትድ ባለፉት ዘጠኝ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።   ተጋጣሚው ኖቲንግሃም ፎረስት በበኩሉ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ዌስትሃም ዩናይትድ እና ኖቲንግሃም ፎረስት ወሳኝ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይፋለማሉ። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያው ዙር እርስ በእርስ ባደረጉት ጨዋታ ዌስትሃም ዩናይትድ 3 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ቶኒ ሃሪንግተን ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ጨዋታውን ይመሩታል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ታህሳስ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ከቡርኪናፋሶ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው  
Jan 6, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 28/2018 (ኢዜአ)፦በአፍሪካ ዋንጫ ወደ ሩብ ፍጻሜ የሚያልፉ ቀሪ ሁለት ሀገራት የሚለዩባቸው ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ።   የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ኮትዲቯር ከቡርኪናፋሶ ጋር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በማራካሽ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኮትዲቯር በምድብ ስድስት በሰባት ነጥብ አንደኛ በመያዝ 16 ውስጥ ገብታለች። ተጋጣሚዋ ቡርኪናፋሶ በምድብ አምስት በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፍ መግባቷን አረጋግጣለች። ግብጽ ለሩብ ፍጻሜ አለፈች ናይጄሪያ ለሩብ ፍጻሜ አለፈች ሁለቱ ጎረቤት ሀገራት በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። አንጎላ እ.አ.አ በ2010 ባዘጋጀችው 27ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሁለት ተገናኝተው ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን እ.አ.አ በ2012 በጣምራ ባዘጋጁት 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በተመሳሳይ በምድብ ሁለት ባደረጉት ጨዋታ ኮትዲቯር 2 ለ 0 አሸንፋለች። ሰለሞን ካሉ እና የቡርኪናፋሶው የቀድሞ ተጫዋች ባካሪ ኮኔ በራሱ ላይ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኮትዲቯር የሁለት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ናት። ቡርኪናፋሶ ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ2013 ባዘጋጀችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለፍጻሜ ደርሳ በናይጄሪያ 1 ለ 0 የተሸፈችበት ውጤት በአህጉራዊ መድረኩ ምርጡ ውጤቷ ነው። ኮትዲቯር የአፍሪካ ዋንጫ ክብሯን የማስጠበቅ ጉዞዋ ለመቀጠል ከቡርኪናፋሶ ጠንካራ ፈተና ይጠብቃታል።   የጨዋታው አሸናፊ ሀገር በሩብ ፍጻሜው ከግብጽ ጋር ይጫወታል። በሌላኛው የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ምሽት አንድ ሰዓት ላይ አልጄሪያ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም ይጫወታሉ። አልጄሪያ በምድብ አምስት በዘጠኝ ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቅ ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ተጋጣሚዋ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በምድብ አራት በሰባት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። ሀገራቱ ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ዋንጫ ሁለት ጊዜ ተገናኝተዋል። ሞሮኮ እ.አ.አ በ1998 ባዘጋጀችው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው አልጄሪያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን (በወቅቱ አጠራሯ ዛየር) 1 ለ 0 አሸንፋለች። አብዱልቃድር ፌርሃዊ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። እ.አ.አ በ2000 በጋና በተካሄደው 22ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሁለት ተገናኝተው ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ከ25 ዓመታት በኋላ በጥሎ ማለፍ የተገናኙት ሁለቱ ሀገራት ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ ጠንካራ ፍልሚያ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። የቡድኖቹ ጨዋታ አሸናፊ ከናይጄሪያ ጋር በሩብ ፍጻሜው ይገናኛል። አዘጋጇ ሞሮኮ፣ ናይጄሪያ፣ ሴኔጋል፣ ካሜሮን፣ ግብጽ እና ማሊ እስከ አሁን ሩብ ፍጻሜ የገቡ ሀገራት ናቸው።
በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ብዙ ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን ያቀበሉ ተጫዋቾች
Jan 5, 2026 138
በእግር ኳስ ጨዋታ ከግብ አስቆጣሪዎች ጀርባ ኳስን ፍትፍት አርገው ጨርሰው የሚያቀብሉ ተጫዋቾች አሉ። አንድ ተጫዋች ግብ ሲያገባ ከማግባቱ ባልተናነሰ ማን ኳሱን አቀበለው? የሚለው ጥያቄ በተመልካቾች ይነሳል። በእግር ኳስ እድገት ውስጥ በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ለጎል ኳስ አመቻችተው የሚያቀብሉ ተጫዋቾች ትልቅ ዋጋ ይሰጣቸዋል። ማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን አሰናበተ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች እየተካሄዱ ይገኛሉ።   የ33 ዓመቱ የሴኔጋል አምበል ሳዲዮ ማኔ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ካስቆጠረው አንድ ግብ በተጨማሪ ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል የቀዳሚነቱን ስፍራ ይዟል። ማኔ ሴኔጋል ለሩብ ፍጻሜ እንድታልፍ ያበረከተው አስተዋጽኦ ትልቅ የሚባል ነው። ስምንት ተጫዋቾች በተመሳሳይ ሁለት ለግብ የሚሆኑ ግቦችን አመቻችተው አቀብለዋል።   ናይጄሪያውያኑ አዴሞላ ሉክማን እና አሌክስ ኢዎቢ፣ የሞሮኮው አዝዲን ኡናሂ፣ የአልጄሪያው አኒስ ሃጂ-ሙሳ፣ የቡርኪናፋሶው ዳንጎ ኡታራ፣ የቱኒዚያው ሃኒባል ሜጅብሪ፣ የደቡብ አፍሪካው ላይል ፎስተር እና የታንዛንያ ኖቫቱስ ሞሮሺ በሁለት ግቦች ላይ እጃቸው ያለበት ተጫዋቾች ናቸው።   የናይጄሪያው የክንፍ የመስመር ተጫዋች አዴሞላ ሉክማን ሁለት ግቦችን በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ አስቆጥሯል።   የኮትዲቯሩ ክርስቶፈር ኦፔሪ እና የናይጄሪያው ሳሙኤል ቹኩዌዜ በተመሳሳይ አንድ አንድ ግቦች ከመረብ ላይ እንዲቆጠሩ የቀጥታ ተሳትፎ አድርገዋል።   የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬን (ካፍ) የዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ኮከብ ተጫዋች ምርጫ ላይ ካስቀመጣቸው መመዘኛ መስፈርቶች አንዱ ማን ብዙ ለጎል የሚሆን አቀበለ? የሚለው ይገኝበታል። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እስከ ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን የግብ አግቢዎችና የኳስ አቀባዮቹ ፉክክር በያዘው ግለት ይቀጥላል ተብሎ ይጠበቃል።
ማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን አሰናበተ 
Jan 5, 2026 108
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 27/2018 (ኢዜአ)፦ ማንችስተር ዩናይትድ የ40 ዓመቱን ፖርቹጋላዊ አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን ከኃላፊነት ማንሳቱን አስታወቀ። አሞሪም ከክለቡ የተለያዩት አመራሮች በሚያስተላልፏቸው ውሳኔዎች ደስተኛ አለመሆናቸውን ትናንት የሰጡትን አስተያየት ተከትሎ መሆኑን ዘ አትሌቲክ ዘግቧል። አሰልጣኙ ላለፉት 14 ወራት በዩናይትድ ቤት ቆይተዋል። በአፍሪካ ዋንጫ ግብጽ ከቤኒን ናይጄሪያ ከሞዛምቢክ ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ ይጫወታሉ   በ3-4-3 የጨዋታ ፍልስፍና ወግ አጥባቂነታቸው ትችት ሲያስተናግዱ የቆዩት አሞሪም ቆይታቸው ውጤታማ አልነበረም። እ.አ.አ 2024 ከፖርቹጋሉ ስፖርቲንግ ሊዝበን የመጡት አሰልጣኙ ትልቁ ውጤታቸው ባለፈው ዓመት ለዩሮፓ ሊግ ፍጻሜ ደርሰው በቶተንሃም ሆትስፐርስ የተሸነፉበት ነው። ዩናይትድ አሞሪምን ማሰናበቱን ተከትሎ የ10 ነጥብ 8 ሚሊዮን ዶላር የውል ማፍረሻ ይከፍላል። የክለቡ የቀድሞ ተጫዋች ዳረን ፍሌቸር ክለቡን በጊዜያዊነት ይመራል። ፍሌቸር ከ18 ዓመት በታች ቡድኑ አሰልጣኝ ሆኖ እየሰራ እንደሚገኝ ይታወቃል። ማንችስተር ዩናይትድ እስከ ዓመቱ መጨረሻ ቋሚ አሰልጣኝ እንደማይቀጥር ዘ አትሌቲክ ዘግቧል።
በአፍሪካ ዋንጫ ግብጽ ከቤኒን ናይጄሪያ ከሞዛምቢክ ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ ይጫወታሉ 
Jan 5, 2026 90
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ የሶስተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ግብጽ ከቤኒን በአጋዲር ስታዲየም ከምሽት አንድ ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሰባት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋ ግብጽ በምድብ ሁለት በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ በመሆን 16 ውስጥ ገብታለች። ተጋጣሚዋ ቤኒን በምድብ አራት በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ በምርጥ ሶስተኝነት ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ዋንጫ አንድ ጊዜ ተገናኝተዋል። አንጎላ እ.አ.አ በ2010 ባዘጋጀችው 27ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሶስት ተገናኝተው ግብጽ በአህመድ ኤልሞሃመዲ እና ኢማድ ሞታይብ ግቦች ቤኒንን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ቡድኖቹ በሁሉም ውድድሮች አራት ጊዜ ተገናኝተው ግብጽ ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። ቤኒን እ.አ.አ በ2019 ግብጽ ባዘጋጀችው 32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ በመግባት በአህጉራዊ መድረክ የተሳትፎ ታሪኳ ምርጡን ውጤቷን አስመዝግባለች። የምዕራብ አፍሪካዋ ቤኒን ለሁለተኛ ጊዜ ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ ከሰባት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ግብጽ ጠንካራ ፈተና ይጠብቃታል። በሌላኛው የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ናይጄሪያ ከሞዛምቢክ ምሽት አራት ሰዓት ላይ በፌዝ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሶስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋ ናይጄሪያ በምድብ ሶስት በዘጠኝ ነጥብ በመሪነት ጨርሳለች። ሞዛምቢክ በምድብ ስድስት በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ መርጥ ሶስተኛ ሆና ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ሁለቱ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። አንጎላ እ.አ.አ በ2010 ባዘጋጀችው 27ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሶስት ተገናኝተው ናይጄሪያ ሞዛምቢክን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ፒተር ኦደምዊንጌ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኦባፌሚ ማርቲንስ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በአፍሪካ ዋንጫ ለአራተኛ ጊዜ እየተሳተፈች የሚገኘው ሞዛምቢክ በእስከ አሁን ተሳትፎዎቿ ከምድቧ አልፋ አታውቅም። የዛሬ ጨዋታዎች አሸናፊዎች በሩብ ፍጻሜው እርስ በእርስ ይገናኛሉ።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
Jan 5, 2026 82
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 27/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ ሳምንት በመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ መድን ከመቀሌ 70 እንደርታ ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በሊጉ ካደረጋቸው 12 ጨዋታዎች መካከል ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ12ቱ ጨዋታዎች ላይ 10 ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎች ተቆጥረውበታል። መድን በ13 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ በበኩሉ እስከ አሁን በሊጉ ያሸነፈው የጨዋታ ብዛት አንድ ብቻ ነው። አምስት ጊዜ ሲሸነፍ ስድስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 13 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 17 ጎሎችን አስተናግዷል። መቀሌ 70 እንደርታ በስምንት ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባህር ዳር ከተማ እስከ አሁን በሊጉ 12 ጨዋታዎችን ያደረገ ሲሆን በሶስቱ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። በስድስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። በ12ቱ ጨዋታዎች ላይ ዘጠኝ ጎሎችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ ዘጠኝ ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ15 ነጥብ 13ተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ ካደረጋቸው 12 ጨዋታዎች መካከል በአራቱ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። አራት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ጥሏል። ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ድሬዳዋ ከተማ በ16 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታሉ።
በተጠባቂው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ እና  ቼልሲ አቻ ተለያዩ
Jan 4, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ20ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ እና ቼልሲ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቲጃኒ ራይንደርስ በ42ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ማንችስተር ሲቲን መሪ አድርጓል። ኢንዞ ፈርናንዴዝ በ94ኛው ደቂቃ ላይ ከመረብ ባሳረፈው ግብ ቼልሲ አቻ ወጥቷል። ባለሜዳው ማንችስተር ሲቲ በኳስ ቁጥጥር እና ኢላማ የጠበቁ ሙከራዎችን በማድረግ የተሻለ ነበር። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ ስድስት ከፍ ብሏል። ቼልሲ በ31 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ሊድስ ዩናይትድ አንድ አቻ ሲለያይ፣ የፉልሃም እና ሊቨርፑል ጨዋታ ሁለት አቻ ተጠናቋል። ብሬንትፎርድ ኤቨርተንን 4 ለ 2፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ክሪስታል ፓላስን 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ሰንደርላንድ አንድ አቻ ተለያይተዋል። የዛሬ ጨዋታዎችን ተከትሎ የ20ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ21ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከታህሳስ 28 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም