ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ሊቨርፑል እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ አቻ ተለያዩ
Mar 15, 2026 129
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት ሊቨርፑል እና ቶተንሃም ሆትስፐርስን ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። ማምሻውን በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ዶምኒክ ስቦዝላይ በ18ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ በቅጣት ምት ያስቆጠረው ግብ ቀያዮቹን መሪ አድርጓል። ሪቻርልሰን በ90ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል ቶተንሃም አንድ ነጥብ አግኝቷል። በጨዋታው ሊቨርፑል የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ቶተንሃም ግልጽ የግብ እድሎችን በመፍጠር ተሽሎ ተገኝቷል። ሊቨርፑል በ49 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አምሰተኛ ከፍ አድርጓል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ለማግኘት በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥሏል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ30 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። የመውረድ አደጋ ውስጥ ያለበት ቶተንሃም ባለፉት 12 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ30ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ አስቶንቪላን 3 ለ 1 አሸንፏል። ክሪስታል ፓላስ ከሊድስ ዩናይትድ፣ ኖቲንግሃም ፎረስት ከፉልሃም ያደረጉት ጨዋታ በተመሳሳይ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የ30ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ነገ ብሬንትፎርድ ከዎልቭስ ጋር በሚያደርጉት ጨዋታ ይጠናቀቃል።
ማንችስተር ዩናይትድ አስቶንቪላን በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል
Mar 15, 2026 125
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ማንችስተር ዩናይትድ አስቶንቪላ 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ካሲሚሮ፣ ማትያስ ኩንሃ እና ቤንጃሚን ሼስኮ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሮስ ባርክሌይ ለአስቶንቪላ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ዩናይትድ በ54 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ዩናይትድ በሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አስቶንቪላ በ51 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቪላ ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። የማንችስተር ዩናይትዱ ብሩኖ ፈርናንዴዝ ዘንድሮ በሊጉ ለግብ አመቻችቶ ያቀበላቸውን ኳሶች ብዛት 16 አድርሷል። በዛሬው ጨዋታም በሁለት ግቦች ላይ ተሳትፎ ነበረው። ይህም ዴቪድ ቤካም በዩናይትድ በአንድ የውድድር ዓመት 15 ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን የማቀበል ክብረ ወሰን እንዲሰብር አድርጎታል። በተመሳሳይ ሰዓት በተደረጉ የ30ኛ ጨዋታዎች ክሪስታል ፓላስ ከሊድስ ዩናይትድ፣ ኖቲንግሃም ፎረስት ከፉልሃም በተመሳሳይ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ በድል ጉዞው ጥሏል
Mar 15, 2026 110
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ24ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ነገሌ አርሲን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሀሰን ሁሴን ግቦቹን አስቆጥሯል። ካሜሮናዊው የነገሌ አርሲ ተጫዋች ፓስካል ኢቡሲ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በሊጉ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ37 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ነገሌ አርሲ በ38 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሁለተኛ ደረጃን ከሃዋሳ ከተማ የመረከብ እድሉን አልተጠቀመበትም። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ-ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ወላይታ ድቻ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። መቀሌ 70 እንደርታ በ23 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። ወላይታ ድቻ በ27 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 24ኛ ሳምንት ተጠናቋል። ፕሪሚየር ሊጉ ኢትዮጵያ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ በምታደርጋቸው የማጣሪያ ጨዋታዎች ምክንያት ይቋረጣል። ውድድሩ መጋቢት 25 ቀን 2018 ዓ.ም በ25ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር እንደሚመለስ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
አትሌት ፎቴን ተስፋይ ለመጀመሪያ ጊዜ ባደረገችው የማራቶን ውድድር አሸነፈች
Mar 15, 2026 70
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በባርሴሎና ማራቶን በሴቶች ውድድር አትሌት ፎቴን ተስፋይ አሸንፋለች። አትሌት ፎቴን ውድድሩን ለማጠናቀቅ 2 ሰዓት ከ10 ደቂቃ ከ53 ሰከንድ ፈጅቶባታል። በዚህም መሠረት የቦታውን ክብረወሰን በመስበር ያሸነፈች ሲሆን፤ በርቀቱ የዓለም ሁለተኛው ፈጣን ሰዓትም አስመዝግባለች። አትሌቷ በመጀመሪያ የማራቶን ውድድሯ ድል ቀንቷታል። በውድድሩ የተሳተፉት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ዘይነባ ይመር ሶስተኛ፣ ጫልቱ ጭምዴሳ አራተኛ እና ያልጋነሽ እስከመች አምስተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድራቸውን አጠናቅቀዋል ። የባርሴሎና ማራቶን በዓለም አትሌቲክስ የነሐስ ደረጃ የተሰጠው የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር ነው።
ቦሌ ክፍለ ከተማ እና አዳማ ከተማ ነጥብ ተጋሩ
Mar 15, 2026 70
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ቦሌ ክፍለ ከተማ እና አዳማ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ፍቅረአዲስ ገዛኸኝ በ34ኛው ደቂቃ ያስቆጠረችው ጎል ቦሌ ክፍለ ከተማን መሪ አድርጓል። ሔለን መሰለ በ62ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈችው ጎል ለአዳማ ከተማ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። የአዳማ ከተማዋ ነጻነት መና የጨዋታው ኮከብ ሆና መርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ ቦሌ ክፍለ ከተማ በ31 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ዛሬ አስቀድሞ በተካሄደ የ19ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ልደታ ክፍለ ከተማን 5 ለ 0 አሸንፏል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሊጉ መሪ ሆነ
Mar 15, 2026 72
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ልደታ ክፍለ ከተማን 5 ለ 0 ረትቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ፤ እሙሽ ዳንኤል ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር እፀገነት ግርማ፣ ንግሥት በቀለ እና ታሪኳ ደቤሶ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሁለት ግቦችን ያስቆጠረችው እሙሽ ዳንኤል የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ 16ኛ ድሉን ያስመዘገበው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ50 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በጊዜያዊነት ተረክቧል። በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ልደታ ክፍለ ከተማ በ15 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል።
በሴኡል ማራቶን ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች በሁለቱም ፆታ አሸነፉ
Mar 15, 2026 73
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ 96ኛው የሴኡል ማራቶን ዛሬ ማለዳ ተካሄዷል። በወንዶች አትሌት ሀፍቱ ተከሉ 2 ሰዓት ከ4 ደቂቃ ከ23 ሴኮንድ አንደኛ ወጥቷል። ነገሌ አርሲ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ይጫወታል አትሌት ሀፍቱ ውድድሩን በአራት ዓመት ውስጥም ለሁለተኛ ጊዜ አሸንፏል። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ጌታነህ ሞላ ሁለተኛ ወጥቷል። አትሌት ፀጋዬ ታደሰ አራተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድሩን አጠናቋል። በሴቶቹ ውድድር ደግሞ አትሌት ሔቨን ኃይሉ 2 ሰዓት ከ19 ደቂቃ ከ10 ሴኮንድ በርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቷን አስመዝግባ አሸንፋለች። አትሌት በቀለች ጉደታ 2ሰዓት ከ19 ደቂቃ ከ40 ሴኮንድ በመግባት ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀች ሲሆን የግል ምርጥ ሰዓቷን አሻሽላለች። አትሌት ቦሰና ሙላቴ ሦስተኛ ወጥታለች። እ.አ.አ በ1931 የተጀመረው የሴኡል ማራቶን በዓለም አትሌቲክስ የፕላቲኒየም ደረጃ የተሰጠው የጎዳና ላይ ውድድር ነው።
ነገሌ አርሲ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ይጫወታል
Mar 15, 2026 70
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 24ኛ ሳምንት ዛሬ በሚደረጉ ጨዋታዎች ይጠናቀቃል። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ነገሌ አርሲ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከልደታ ክፍለ ከተማ ጋር ይጫወታል ነገሌ አርሲ በውድድር ዓመቱ 23 ጨዋታዎችን አከናውኖ በ10ሩ ሲያሸንፍ አምስት ጊዜ ተሸንፏል። በስምንት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 22 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 14 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ነገሌ አርሲ በ38 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 23 ጨዋታዎች ስምንቱን ሲያሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪው 10 ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 17 ግቦችን ሲያስቆጥር 13 ግቦችን አስተናግዷል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ34 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ነገሌ አርሲ ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ካሸነፈ ሁለተኛ ደረጃን ከሃዋሳ ከተማ ይረከባል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ካሸነፈ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። በሌላኛው መርሐ-ግብር መቀሌ 70 እንደርታ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቀሌ 70 እንደርታ በውድድር ዓመቱ ባካሄዳቸው 23 ጨዋታዎች አራቱን አሸንፎ በዘጠኙ ተሸንፎ 10 ጊዜ አቻ ተለያይቷል።15 ግቦችን ሲያስቆጥር 25 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ22 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው ወላይታ ድቻ በሊጉ ካደረጋቸው 23 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን በድል ሲወጣ ሰባት ጊዜ ተሸንፏል። በ11 ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በ23ቱ ጨዋታዎች ላይ 26 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ በተመሳሳይ 26 ጎሎች ገብተውበታል። ወላይታ ድቻ በ26 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። መቀሌ 70 እንደርታ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ቡድኑ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታል። በ23ኛ ሳምንት የሊጉን መሪ ሲዳማ ቡናን 3 ለ 1 ያሸነፈው ወላይታ ድቻ በበኩሉ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይፋለማል።
የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከልደታ ክፍለ ከተማ ጋር ይጫወታል
Mar 15, 2026 76
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። ከቀኑ 7 ሰዓት ልደታ ክፍለ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ በንክ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ልደታ ክፍለ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው 18 ጨዋታዎች መካከል ያሸነፈው አራት ብቻ ነው። በ11ዱ ሲሸነፍ በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 21 ግቦችን ሲያስቆጥር 34 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ15 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በበኩሉ በ18 ጨዋታዎች 15 ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 47 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ሰባት ጎሎች ተቆጥረውበታል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ47 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ንግድ ባንክ በሊጉ ከፍተኛ የግብ መጠን ያስቆጠረ እና አነስተኛ ጎል ያስተናገደ ክለብ ነው። ልደታ ክፍለ ከተማ በ17ኛ ሳምንት በሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ካስተናገደው የ4 ለ 2 ሽንፈት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ የሊጉን መሪነት በጊዜያዊነት ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ይረከባል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ቦሌ ክፍለ ከተማ ከአዳማ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቦሌ ክፍለ ከተማ በሊጉ 18 ጨዋታዎች አድርጎ ስምንት ጊዜ ድል ሲቀናው በአራቱ ተሸንፏል። በቀሪ ስድስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 22 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 17 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ30 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 18 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ብቻ ያሸነፈው አዳማ ከተማ በስምንቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። በ18ቱ ጨዋታዎች 13 ግቦችን ሲያስቆጥር 27 ጎሎችን አስተናግዷል። አዳማ ከተማ በ20 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቦሌ ክፍለ ከተማ ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። አዳማ ከተማ ካሸነፈ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት እስከ መጋቢት 8 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ49 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። አርባምንጭ ከተማ እና አዲስ አበባ ከተማ 13ኛ እና 14ተኛ ደረጃን ይዘው ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሉ። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን በ22 ግቦች ትመራለች። ረድኤት አስረሳኸኝ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ13 ጎሎች ትከተላለች።
ማንችስተር ዩናይትድ ከአስቶንቪላ የሚያደርጉት የሊግ ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Mar 15, 2026 87
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በኦልድትራፎርድ ስታዲየም ማንችስተር ዩናይትድ ከአስቶንቪላ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ማንችስተር ዩናይትድ በ51 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። አስቶንቪላ በተመሳሳይ 51 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በማይክል ካሪክ የሚመራው ማንችስተር ዩናይትድ በ29ኛ ሳምንት በኒውካስትል ዩናይትድ የ2 ለ 1 ሽንፈት አስተናግዷል። ውጤቱ ዩናይትድ በካሪክ ስር ያስተናገደው የመጀመሪያ የሊግ ሽንፈት ነው። ተጋጣሚው አስቶንቪላ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች በቼልሲ እና ዎልቭስ ሽንፈት አስተናግዷል። ጨዋታው በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ለማድረግ ለሚፎካካሩት ክለቦች ወሳኝ የሚባል ነው። የ47 ዓመቱ አንቶኒ ቴይለር ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ሊቨርፑል ከቶተንሃም ሆትስፐርስ ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሊቨርፑል በ48 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ቀያዮቹ በ29ኛ ሳምንት በዎልቭስ ያልተጠበቀ የ2 ለ 1 ሽንፈት ማስተናገዳቸው የሚታወስ ነው። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ29 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በውጤት ማጣት ቀውስ ውስጥ የሚገኘው ቶተንሃም ሆትስፐርስ ባለፉት 11 የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ጨዋታው ለወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል በሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በሚያደርገው ጉዞ ወሳኝ ነው። የመውረድ ስጋት ያንዣበበት ቶተንሃም ሶስት ነጥብ መጠነኛ የሆነ እፎይታ ይሰጠዋል። ክሪስታል ፓላስ ከሊድስ ዩናይትድ እና ኖቲንግሃም ፎረስት ከፉልሃም በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
ማንችስተር ሲቲ ነጥብ ጣለ
Mar 15, 2026 69
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዌስትሃም ዩናይትድ እና ማንችስተር ሲቲ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በለንደን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በርናንዶ ሲልቫ በ31ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ ማንችስተር ሲቲ መሪ ሆኗል። ኮንስታንቲኖስ ማቭሮፓኖስ በ35ኛው ደቂቃ የዌስትሃምን የአቻነት ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ማንችስተር ሲቲ ብልጫ ቢወስድም ተጨማሪ ጎል ማስቆጠር አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ አንድ ተስተካካይ የሚቀረው ማንችስተር ሲቲ በ61 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ ዘጠኝ ከፍ ብሏል። ውሃ ሰማያዊዎቹ ነጥብ መጣላቸውን ተከትሎ የዋንጫ የማንሳት እድላቸው የጠበበ ሆኗል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ30 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ወደ 17ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና የወጣበትን ወሳኝ አንድ ነጥብ አግኝቷል። ዌስትሃም ከሶስት ወራት በኋላ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። የሊጉ መሪ አርሰናል ኤቨርተንን 2 ለ 0 አሸንፏል።
አርሰናል ኤቨርተንን በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Mar 14, 2026 174
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት አርሰናል ኤቨርተንን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቪክቶር ዮኮሬስ በ89ኛው እና ማክስ ዶውማን በ97ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። በሊጉ 21ኛ ድሉን ያስመዘገበው አርሰናል በ70 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ 10 ከፍ አድርጓል። መድፈኞቹ በተፈተኑበት ጨዋታ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝተዋል። ተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በለንደን ስታዲየም ከዌስትሃም ዩናይትድ ጋር የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። በሌላኛው መርሐ-ግብር ኒውካስትል ዩናይትድ ቼልሲን 1 ለ 0 አሸንፏል። አንቶኒ ጎርደን የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል።
በተጠባቂው ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሃዋሳ ከተማን አሸነፈ
Mar 14, 2026 160
አዲስ አበባ ፤ መጋቢት 5 /2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ24ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሃዋሳ ከተማን 4 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ናትናኤል ዳንኤል፣ ሁዘይፋ ሻፊ እና ዩጋንዳዊው ሳይመን ፒተር በጨዋታ፣ አዲስ ግደይ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጌታነህ ከበደ እና ሽመልስ በቀለ ለሃዋሳ ከተማ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ30 ነጥብ ደረጃውን ከ13ኛ ወደ 10ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሃዋሳ ከተማ በበኩሉ በ40 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ሃዋሳ ከተማ ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማጥበብ እድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የፊት መስመር ተሰላፊ አዲስ ግደይ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ 10 ከፍ በማድረግ ተመሳሳይ ግብ ካስቆጠረው የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው ጋር የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በጋራ መምራት ችሏል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ኢትዮጵያ ቡና አዳማ ከተማን 3 ለ 2 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ጨዋታ ዘላለም አባተ፣ በፍቃዱ አለማየሁ እና ሀምዛ ሱልጣን ለቡናማዎቹ ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አሕመድ ሁሴን ለአዳማ ከተማ ግቦቹን አስቆጥሯል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን ያሳካው ኢትዮጵያ ቡና አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ32 ነጥብ ደረጃውን ከ10ኛ ወደ 8ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በሊጉ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ቀን ላይ በተደረጉ የ24ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን አርባምንጭ ከተማን 2 ለ 0፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ድሬዳዋ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
በፕሪሚየር ሊጉ ብራይተን ድል ሲቀናው በርንሌይ እና ቦርንማውዝ አቻ ተለያይተዋል
Mar 14, 2026 138
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5 /2018(ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዛሬ ማምሻውን ተጀምሯል። በስታዲየም ኦፍ ላይት በተደረገው ጨዋታ ብራይተን ሰንደርላንድን 1 ለ 0 ተሸንፏል። ያንኩባ ሚንቴ በ58ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። የሰንደርላንዱ ክሪስ ሪግ በ50ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል በቪዳዮ በታገዛ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ተሽሯል። በሊጉ 10ኛ ድሉን ያስመዘገበው ብራይተን በ40 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሰንደርላንድ በተመሳሳይ 40 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በተርፍሙር ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ በርንሌይ እና ቦርንማውዝ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ውጤቱን ተከትሎ በርንሌይ በ20 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቦርንማውዝ በ41 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 የሊጉ መሪ አርሰናል ከኤቨርተን፣ ዌስትሃም ዩናይትድ ከማንችስተር ሲቲ ምሽት አምስት ላይ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ተጠባቂ ናቸው።
ኢትዮጵያ መድን እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ድል ቀንቷቸዋል
Mar 14, 2026 77
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 24ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች በመካሄድ ላይ ናቸው። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን አርባምንጭ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ወገኔ ገዛኸኝ እና አማኑኤል ኤርቦ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ከሁለት የአቻ ውጤቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮጵያ መድን በ28 ነጥብ ደረጃውን ከ16ኛ ወደ 12ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ19 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሐ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርስቲ ድሬዳዋ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳዊት ገብሩ በ10ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የድሬዳዋ ከተማው ተከላካይ ሲያም ሱልጣን በ84ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ28 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ወደ 13ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። በአንጻሩ በሊጉ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በተመሳሳይ 28 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ከነበረበት 12ኛ ደረጃ ወደ 14ኛ ዝቅ ብሏል።
ለ"ፊቼ ጫምባላላ" በዓል የሚካሄደው ስፖርታዊ ውድድር በዓሉንና ባህላዊ እሴቶቹን ለማስተዋወቅ እያገዘ ነው
Mar 14, 2026 76
ሀዋሳ፤ መጋቢት 5/2018 (ኢዜአ)፡-የሲዳማ ዘመን መለወጫ "ፊቼ ጫምባላላ"ን በማስመልከት በየዓመቱ የሚካሄደው ስፖርታዊ ውድድር በዓሉንና ባህላዊ እሴቶቹን ለማስተዋወቅና ለማጠናከር እያገዘ መሆኑ ተገለጸ። ለ"ፊቼ ጫምባላላ እሮጣለሁ" በሚል መሪ ቃል ዛሬ በሀዋሳ ከተማ የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር ተካሂዷል፡፡ በመርሀግብሩ መሰረትም በወንዶች የ10 ሺህ ሜትር፤ በሴቶች ደግሞ የ5 ሺህ ሜትርና የሕፃናት ውድድሮች ተካሂደዋል፡፡ በውድድሩ ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶማርሶ ዶና በዓሉን ምክንያት በማድረግ በየዓመቱ የሚካሄደው ውድድር የፊቼ ጫምባላላን በዓል ከማድመቅ ባለፈ በውስጡ ያሉትን የአብሮነትና የሠላም እሴቶች ለማስተዋወቅና ለማጠናከር እያገዘ መሆኑን ተናግረዋል። በዛሬው ስፖርታዊ ውድድርም ከክልሉና ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የመጡ አንጋፋና አዳዲስ አትሌቶች መሳተፋቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ይህም አዳዲሶቹ ከነባሮቹ ልምድ እንዲቀስሙ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የአካባቢውን አትሌቲክስ ይበልጥ ለማነቃቃት ጠቃሚ መሆኑን አስረድተዋል። ውድድሩን ያዘጋጀው የ“ብራይት አፍሪካ ራን” መስራችና ሥራ አስኪያጅ ካሳሁን ካቢሶ በበኩላቸው በዓሉን ምክንያት በማድረግ ውድድሩ ዘንድሮ ለአራተኛ ጊዜ መካሄዱን ተናግረዋል። በቀጣይ ወደ ፕሮፌሽናል ውድድር እያደገ እንደሚሄድ ጠቁመው፣ ውድድሩ የ"ፊቼ ጫምባላላ" በዓልን ለዓለም በማሳየት ረገድ ጉልህ ድርሻ እንዳለውና ዘንድሮም በተሳካ ድምቀት መከናወኑን ተናግረዋል፡፡ በሁለቱም ርቀት በተካሄዱ ውድድሮች አንደኛ የወጡ አትሌቶች የሜዳልያና የ30 ሺህ ብር ሽልማት ሲያገኙ እስከ 10ኛ ደረጃን የያዙትም የተለያየ መጠን ያለው ገንዘብና የሜዳሊያ ሽልማት እንደተበረከተላቸው ገልጸዋል። በወንዶች 10 ሺህ ሜትር አንደኛ የወጣው አትሌት አብዱልመጂድ አባደላ ውድድሩን ቀዳሚ ሆኖ ማጠናቀቅ በመቻሉ ደስታ እንደተሰማው ተናግሯል፡፡ ውድድሩ ለበዓሉ ድምቀት የራሱን አስተዋጾ ማድረጉን ጠቅሶ፣ በውድድሩ ከተለያዩ አካባቢዎች ከመጡ አትሌቶችና ከሀዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ጋር መታደሙ ልዩ ስሜት እንደፈጠረለት ተናግሯል፡፡ የሀዋሳ አየርና ጎዳናው ለውድድሩ ምቹ እንደነበር የተናገረችው ደግሞ በሴቶች የ5 ሺህ ሜትር ውድድር አንደኛ የወጣችው አትሌት እመቤት ሽብሩ ናት፡፡ ውድድሩ ብቃቷን ለመገምገም ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላት ጠቁማ፣ እንዲህ ያሉ ውድድሮች ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት ሚናቸው የጎላ በመሆኑ መጠናከር አለባቸው ብላለች። በጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር የሲዳማ ክልልና የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡
በፕሪሚየር ሊጉ አርሰናል ከኤቨርተን ማንችስተር ሲቲ ከዌስትሃም ዩናይትድ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Mar 14, 2026 116
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 30ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። በዕለቱ አምስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ አርሰናል ኤቨርተንን በኤምሬትስ ስታዲየም ያስተናግዳል። አርሰናል በ67 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ኤቨርተን በ43 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው አርሰናል የሊጉን መሪነት ለማጠናከር፣ ኤቨርተን ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ የሚያደርጉት ነው። የ42 ዓመቱ አንዲ ማድሊ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ዌስትሃም ዩናይትድ ከማንችስተር ሲቲ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በለንደን ስታዲየም ይጫወታሉ። ዌስትሃም ዩናይትድ በ28 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ማንችስተር ሲቲ በ60 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ዌስትሃም ዩናይትድ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ትግል ሶስት ነጥብ ማግኘት ወሳኝ ነው። ማንችስተር ሲቲ በዋንጫው ፉክክር ለመቆየት ጨዋታውን ማሸነፍ ይጠበቅበታል። የ41 ዓመቱ ማይክል ኦሊቨር የጨዋታው መሐል ዳኛ ናቸው። ቼልሲ ከኒውካስትል ዩናይትድ ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ይጫወታሉ። የምዕራብ ለንደኑ ቼልሲ በ48 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ኒውካስትል ዩናይትድ በ39 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቼልሲ የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ውጥኑን ለማስቀጠል፣ ኒውካስትል ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። በርንሌይ ከቦርንማውዝ እና ሰንደርላንድ ከብራይተን በተመሳሳይ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ሃዋሳ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Mar 14, 2026 79
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 24ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ።’ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሃዋሳ ከተማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በውድድር ዓመቱ እስከ አሁን ባደረጋቸው 23 ጨዋታዎች ስድስቱን ሲያሸንፍ ስምንት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ዘጠኝ ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 28 ግቦችን ሲያስቆጥር 30 ግቦችን አስተናግዷል። የ2016 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ27 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሃዋሳ ከተማ በሊጉ ባከናወናቸው 23 ጨዋታዎች በ11ዱ ድል ሲቀናው በአምስት ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። በሰባት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 26 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 14 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሃዋሳ ከተማ በ42 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ሁለቱም ቡድኖች ተከታታይ ድላቸውን ለማስመዝገብ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። ሃዋሳ ከተማ ካሸነፈ ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ ያደርጋል። በተያያዘም በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም አርባምንጭ ከተማ ከኢትዮጵያ መድን ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው 23 ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው ሶስት ጊዜ ብቻ ነው። 10 ጊዜ ሲሸነፍ በተመሳሳይ 10 ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። በ23 ጨዋታዎች 16 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 27 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ19 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን ካደረጋቸው ጨዋታዎች በአምስቱ ድል ሲቀናው ስምንት ጊዜ ተሸንፏል። 10 ጊዜ አቻ ወጥቷል። 17 ግቦችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ 18 ጎሎች ተቆጥረውበታል። መድን በ25 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። አርባምንጭ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ኢትዮጵያ መድን ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። ኢትዮጵያ ቡና ከአዳማ ከተማ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቡናማዎቹ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀራቸው በ29 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዘዋል። አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱም ቡድኖች በ23ኛ ሳምንት ካስተናገዱት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ-ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ25 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ድሬዳዋ ከተማ በ28 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። በ23ኛ ሳምንት ወልዋሎ ከመቻል ጋር ያለ ግብ አቻ ሲለያይ ድሬዳዋ ከተማ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የ2 ለ 1 ሽንፈት አስተናግዷል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታሉ።
ሲዳማ ቡና ምድረ ገነት ሽሬን በማሸነፍ መሪነቱን አጠናከረ
Mar 13, 2026 136
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 24ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሲዳማ ቡና ምድረ ገነት ሽሬን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብርሃኑ በቀለ እና አዲስ ፈራሚው አቤል ያለው ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሲዳማ ቡና ነጥቡን ወደ 45 ከፍ በማድረግ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ ሃዋሳ ከተማ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 12ኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በአንጻሩ በሊጉ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ምድረ ገነት ሽሬ በ27 ነጥብ 14ተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። በዝውውር መስኮቱ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ሲዳማ ቡና ያመራው አቤል ያለው በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ 10 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን መምራት ጀምሯል። ለሲዳማ ቡና በሁለት ጨዋታዎች ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ባህርዳር ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አንተነህ ተፈራ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ባህር ዳር ከተማ በ31 ነጥብ ደረጃውን ከ10ኛ ወደ 8ኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቅዱስ ጊዮርጊስ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ25 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ስምንት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ24ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ሸገር ከተማ ሀዲያ ሆሳዕናን 2 ለ 0 ሲያሸንፍ ፋሲል ከነማ እና መቻል ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ሸገር ከተማ ተከታታይ ድሉን አስመዘገበ
Mar 13, 2026 80
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 4/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 24ኛ ሳምንት ዛሬ ተጀምሯል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሸገር ከተማ ሀዲያ ሆሳዕናን 2 ለ 0 አሸንፏል። አሚር አብዶ እና ሚሊዮን ኃይሉ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሊጉ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው ሸገር ከተማ በ30 ነጥብ ደረጃውን ከ14ኛ ወደ 8ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሀዲያ ሆሳዕና በ29 ነጥብ ከነበረበት 9ኛ ደረጃ ወደ 10ኛ ዝቅ ብሏል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ፋሲል ከነማ እና መቻል ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ፋሲል ከነማ በ35 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አምስተኛ ከፍ አድርጓል። ቡድኑ ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። መቻል በ36 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከምድረ ገነት ሽሬ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከባህር ዳር ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተመሳሳይ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።