ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል
Apr 18, 2026 35
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 10 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ፋሲል ከነማ ከመቀሌ 70 እንደርታ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ፋሲል ከነማ በ42 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። መቀሌ 70 እንደርታ በ26 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ያሸነፈው ፋሲል ከነማ በድል ጉዞው ለመቀጠል ይጫወታል። ካሸነፈ የሁለተኝነት ደረጃን ከመቻል የመረከብ እድል ያገኛል። በ27ኛ ሳምንት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን 2 ለ 1 ያሸነፈው መቀሌ 70 እንደርታ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይፋለማል። ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት ለሚያደርገው ትግል ወሳኝ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ምሽት 12 ሰዓት ላይ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ29 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ34 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ወልዋሎ ማሸነፍ ላለመውረድ በሚያደርገው ትግል ወሳኝ የሚባል ነው። በ27ኛ ሳምንት በሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና 1 ለ 0 የተሸነፈው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት እስከ ሚያዚያ 13 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ሲዳማ ቡና በ51 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። አቤል ያለው ከሲዳማ ቡና በ12 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ይገኛል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ አዲስ ግደይ በ10 ጎሎች ይከተላል።
የመዲናዋ የልማት እመርታ የኢትዮጵያን ገፅታ በማጉላት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 18, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፡- የአዲስ አበባ ከተማ የልማት እመርታ የኢትዮጵያን ስምና ገፅታ በማጉላት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ አርባ ስድስት ሜዳ ተብሎ የሚጠራውን የስፖርት ማዘውተሪያ መርቀው ለህዝብ አገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የአዲስ አበባ ወጣቶች ስፖርት ወዳድ መሆናቸውን አስተዳደሩ በፅኑ እንደሚረዳ ገልጸዋል። በዚህም ወጣቶች ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ማዘውተሪያ ቦታ እንዲያገኙ ለማስቻል በየሰፈሩ የስፖርት መሠረተ ልማት በስፋት እየተገቡ መሆኑን ገልጸዋል። በመዲናዋ የሚገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ወጣቶችን በአካልና በአዕምሮ እንዲጎለብቱ ለማስቻል መሆኑንም ተናግረዋል። የአዲስ አበባ የስብዕና መገንቢያ ማዕከላትም የኢትዮጵያን ርዕይ የሚያሳካ ብቁና ጤናማ ትውልድ ለመቅረፅ ጉልህ ጠቀሜታ እንዳላቸው አስገንዝበዋል። መዲናዋም የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትና ፍላጎት ታሳቢ በማድረግ እየተሰራች መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልፅግና ግዞ የሚያቆም አንዳች ኃይል የለም፤ ልማታችንም በታላቅ ቁጭትና ወኔ አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። በአዲስ አበባ መጪውን ትውልድ ታሳቢ በማድረግ የሚገነቡ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችም የኢትዮጵያን ስምና ገፅታ በማጉላት ወሳኝ ሚና እያበረከቱ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የልማት እመርታዎች ዕዳን ወደ ምንዳ በመቀየር ለሀገር ሁለንተናዊ ብልፅግና መሠረት እየጣሉ መሆኑን ጠቅሰዋል። በቀጣይም የአዲስ አበባ ነዋሪዎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ምቹ፣ ጽዱና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያጎናፅፉ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
የቼልሲ እና ማንችስተር ዩናይትድ የሊጉ ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Apr 18, 2026 60
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። በዕለቱ አምስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት አራት ሰአት ላይ ቼልሲ ከማንችስተር ዩናይትድ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቼልሲ በ48 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ዩናይትድ በ55 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የምዕራብ ለንደኑ ክለብ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ቡድኑ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመግባት ያለውን ተስፋ ለማለምለም ጨዋታውን ማሸነፍ ግድ ይለዋል። በ32ኛ ሳምንት በሊድስ ዩናይትድ 2 ለ 1 የተሸነፈው ማንችስተር ዩናይትድ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ማንችስተር ዩናይትድ ማሸነፍ የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን ለማረጋገጥ የበለጠ ይቃረባል። በሌላኛው መርሐ ግብር ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከብራይተን ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ። የሰሜን ለንደኑ ቶተንሃም በ30 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ብራይተን በ46 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት 14 የሊግ ጨዋታዎች ድል የናፈቀው ቶተንሃም ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት የዛሬውን ጨዋታ ማሸነፍ ይጠበቅበታል። ብራይተን ካሸነፈ በሊጉ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። ከቀኑ 8 ሰዓት ከ30 ላይ ብሬንትፎርድ ከፉልሃም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሊድስ ዩናይትድ ከዎልቭስ፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ከቦርንማውዝ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
አትሌት ፋንታዬ አዳነ የ10 ሺህ ሜትር የሴቶች ውድድርን አሸነፈች
Apr 18, 2026 50
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በ10 ሺህ ሜትር የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ውድድርን አትሌት ፋንታዬ አዳነ በበላይነት አጠናቅቃለች። የአለም አትሌትክስ የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ የአንድ ቀን ውድድር በአዲስ አበባ ስታዲየም እየተካሄደ ነው። በዚህ ውድድር ፋንታዬ አዳነ የ10 ሺህ ሜትር የሴቶች ፍጻሜ ውድድርን በአንደኝነት አጠናቃለች። አትሌት አልማዝ ባራኪ አትሌት ጥበብ እንየው ሁለተኛ እና ሶስተኛ ሆነው አጠናቀዋል።
የዓለም አትሌቲክስ የአንድ ቀን ውድድር መካሄድ ጀመረ
Apr 18, 2026 53
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10 /2018 (ኢዜአ)፡- የዓለም አትሌቲክስ የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ የአንድ ቀን ውድድር በአዲስ አበባ ስታዲየም መካሄድ ጀምሯል። ውድድሩ የኢትዮጵያ አትሌቶች ብቻ የሚሳተፉበት እና ዓለም አቀፍ አትሌቶች የሚሳተፉበት በሚል ለሁለት ተከፍሏል። ታሪካዊው ውድድር በሴቶች የ10 ሺህ ሜትር ፍጻሜ ተጀምሯል። በውድድሩ ላይ አፍሪካ፣ አውሮፓ፣ እስያ እና ሰሜን አሜሪካን ጨምሮ ከተለያዩ አህጉራት የተወጣጡ ከ70 በላይ አትሌቶች ይሳተፋሉ። አሜሪካዊቷ ጋቢ ቶማስ እና ኬንያዊው ፈርዲናንድ ኦማኒያላ በውድድሩ ላይ ከሚሳተፉ ታዋቂ አትሌቶች መካከል ይጠቀሳሉ። ውድድሩ በተለያዩ ርቀቶች ይካሄዳል። የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የዓለም አትሌቲክስ የነሀስ ደረጃ የተሰጠው ነው። ውድድሩ ከተለያዩ ሀገራት የተውጣጡ አትሌቶች የሚሳተፉበት ከመሆኑ ባሻገር አሸናፊ የሚሆኑ አትሌቶች ከፍተኛ ሽልማት እንደሚያገኙ የዓለም አትሌቲክስ አስታውቋል። የአንድ ቀን ውድድሩ የዓለም አትሌቲክስ ዓመታዊ የኢንተኮንቲነንታል ውድድር አካል ነው።
ህድአት ካሡ ከፓራጓይዋ አሊሰን ባሬሮ ጋር የአውሮፓ ወዳጅነት ዋንጫን በጋራ ከፍተኛ ግብ አግቢነት አጠናቀቀች
Apr 17, 2026 425
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በቱርክዬ አስተናጋጅነት ከመጋቢት 28 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በተካሄደው የዩኤፋ (UEFA) ከ18 ዓመት በታች ሴቶች የወዳኝነት ዋንጫ ዛሬ ተጠናቋል። በውድድሩ ላይ የተሳተፈው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አራተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። በውድድሩ ማጠቃለያ ላይ የደቡብ አሜሪካዋ ተወካይ ፓራጓይ የወርቅ ሜዳሊያና የዋንጫ ባለቤት በመሆን ቀዳሚውን ደረጃ ስትይዝ፤ ኖርዌይ ሁለተኛ እንዲሁም አስተናጋጇ ቱርክዬ ሦስተኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል። ኢትዮጵያ በበኩሏ ውድድሩን በአራተኛነት በማጠናቀቋ ለብሔራዊ ቡድኑ የተሳትፎ ሜዳሊያ ተበርክቶለታል። በግል ብቃት ረገድ ኢትዮጵያዊቷ ተጫዋች ህድአት ካሡ ደምቃ የታየች ሲሆን፤ በውድድሩ ወቅት አራትግቦችን በማስቆጠር ከፓራጓይዋ አሊሰን ባሬሮ ጋር በእኩልነት የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ በመሆን ማጠናቀቋን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በተጨማሪም የውድድሩ ኮከብ ተሸላሚዎች ይፋ ሲሆኑ፤ ፓራጓይ ከዋንጫ አሸናፊነቷ ጎን ለጎን የግል ሽልማቶችንም ጠቅልላለች። በዚህም ታማራ አማሪላ የውድድሩ ኮከብ ግብ ጠባቂ ተብላ ስትመረጥ፤ ሲናትሂያ ካስኮ ደግሞ የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች በመሆን ተሸልማለች።
ፓራጓይ የአውሮፓ ወዳጅነት ዋንጫን አነሳች
Apr 17, 2026 331
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ):- የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ያዘጋጀው እና በቱርኪዬ ሲካሄድ የቆየው የ"UEFA Frendship Cup" ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ውድድር ዛሬ ተጠናቋል። በፍጻሜው ጨዋታ ፓራጓይ ኖርዌይን 1 ለ 0 በመርታት የውድድሩ አሸናፊ ሆናለች። በውድድሩ ላይ የተሳተፈው የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዛሬ ባደረገው ጨዋታ በቱርኪዬ ተሸንፎ አራተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። ቱርኪዬ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ኮስታሪካ ሞሮኮን በመለያ ምት 5 ለ 4 በመርታት አምስተኛ ሆና ስትጨርስ ሞሮኮ ስድስተኛ ደረጃን ይዛለች። ዩራጓይ ኡዝቤኪስታንን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት በማሸነፍ ሰባተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በውድድሩ በሁሉም ጨዋታዎች ሽንፈት ያስተናገደችው ኡዝቤኪስታን የመጨረሻውን ስምንተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ከመጋቢት 28 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ሲያካሂድ የቆየው የወዳጅነት ዋንጫ ከውድድር ባለፈ የክፍለ አህጉራዊ እግር ኳስ ልማት ትብብርን ማጠናከርን ያለመ ነው። በተጨማሪም የእርስ በእርስ የልምምድ ልውውጥ የተደረገ ሲሆን የተለያዩ ስልጠናዎች እና ጉብኝቶችም የውድድሩ አካል ነበሩ።
ኢትዮጵያ በአውሮፓ ወዳጅነት ዋንጫ አራተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቀቀች
Apr 17, 2026 127
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ):- የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ያዘጋጀው የ"UEFA Frendship Cup" ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ውድድር የማጠቃለያ ጨዋታዎች በመካሄድ ላይ ይገኛሉ። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዛሬ ለደረጃ ባደረገው ጨዋታ በቱርኪዬ 3 ለ 1 ተሸንፏል። ምትኬ ብርሃኑ ለኢትዮጵያ ብቸኛውን ጎል አስቆጥራለች። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ አራተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ቱርኪዬ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። በቻለው ለሜቻ የሚመራው የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በውድድሩ ላይ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሁለቱን ሲያሸንፍ በተመሳሳይ በሁለቱ ሽንፈት አስተናግዷል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የቀሪ ሳምንታት መርሐ ግብር ይፋ ሆነ
Apr 17, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበር የ2018 የውድድር ዘመን መጠናቀቂያ የሆኑትን ከ29ኛ እስከ 38ኛ ሳምንት ያሉ የጨዋታ መርሐ ግብሮችን ይፋ አድርጓል። እንደ አክሲዮን ማህበሩ መግለጫ ከሆነ፣ የሊጉ ውድድር የሚቀጥለው የኢትዮጵያ ዋንጫ ጨዋታዎች ከተከናወኑ በኋላ ሲሆን፣ ሚያዝያ 21 ቀን 2018 ዓ.ም ዳግም እንደሚጀመር ታውቋል። ይህ የቀሪ አሥር ሳምንታት መርሃ ግብር የሊጉን ሙሉ የውድድር ጉዞ የሚያጠቃልል ነው። የቀሩት ሳምንታት ጨዋታዎች በሁለት የሀገሪቱ ስታዲየሞች እንደሚከናወኑ የተገለጸ ሲሆን፣ ጨዋታዎቹም በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየምና በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳሉ። የኢትዮጵያ ዋንጫ የጨዋታ ሁኔታን ታሳቢ በማድረግ የ33ኛ እና የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብሮች ላይ ማሻሻያ ሊደረግ እንደሚችል ማህበሩ አመልክቷል። በተጨማሪም፣ የውድድር ዘመኑ ማጠቃለያ የሆኑት የ37ኛ እና የ38ኛ ሳምንት ጨዋታዎች የክለቦችን የደረጃ እና የውጤት ፉክክር መሰረት በማድረግ ለውጥ ሊደረግባቸው እንደሚችልም ተገልጿል።
ኢትዮጵያ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ለማጠናቀቅ ከቱርኪዬ ጋር ዛሬ ትጫወታለች
Apr 17, 2026 167
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ያዘጋጀው የ"UEFA Frendship Cup" ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ውድድር ዛሬ ይጠናቀቃል። ውድድሩ በቱርኪዬ ከመጋቢት 28 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ሲካሄድ ቆይቷል። በወዳጅነት ዋንጫው ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ ስምንት ሀገራት ተሳትፈዋል። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ለማጠናቀቅ ከቱርኪዬ ጋር ዛሬ ከቀኑ ስምንት ሰዓት ላይ ትጫወታለች። በምድብ ሁለት ጨዋታዋን ያደረገችው ኢትዮጵያ በምድቧ ሶስት ጨዋታዎችን አድርጋ ሁለቱን ስታሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥተዋል። በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በምድብ አንድ የተደለደለችው ቱርኪዬ በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። በአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር የውድድር ደንብ መሰረት ከየምድቡ ሁለተኛ የወጡ ሀገራት ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ይጫወታሉ። ከጨዋታው በፊት ብሔራዊ ቡድኑ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት ማከናወኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በአሰልጣኝ ቻለው ለሜቻ የሚመራው ቡድን በውድድሩ ላይ ጥሩ እንቅስቃሴ አድርጓል። ብሔራዊ ቡድኑ መልካም ጉዞውን ለማሳመር ከቱርኪዬ ጋር ለደረጃ ይጫወታል። ከየምድቡ አንደኛ የወጡት ፓራጓይ እና ኖርዌይ ዋንጫውን ለማንሳት ዛሬ ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ፣ ኮስታሪካ፣ ዩራጓይ፣ ኖርዌይ፣ ቱርኪዬ፣ ፓራጓይ፣ ሞሮኮ እና ኡዝቤኪስታን በውድድሩ ላይ የተሳተፉ ሀገራት ናቸው። የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ያዘጋጀው የወዳጅነት ዋንጫ ከውድድር ባለፈ የክፍለ አህጉራዊ እግር ኳስ ልማት ትብብርን ማጠናከርን ያለመ ነው። በተጨማሪም የእርስ በእርስ የልምምድ ልውውጥ የተደረገ ሲሆን የተለያዩ ስልጠናዎች እና ጉብኝቶችም የውድድሩ አካል ነበሩ።
በያዝነው ወር ሶስት ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ኩነቶች አዲስ አበባ ይካሄዳሉ
Apr 16, 2026 193
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 8/2018(ኢዜአ)፦ዓለም አቀፉ አዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአትሌቲክስ ውድድርን ጨምሮ አዲስ አበባ ውስጥ በሚያዚያ ወር ሶስት ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ኩነቶች ይካሄዳሉ። ከሚካሄዱት ዓለምአቀፍ ስፖርታዊ ኩነቶች ውስጥ አንዱ የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአንድ ቀን የአትሌቲክስ ውድድር በመጪው ቅዳሜ ይካሄዳል። ይህ ውድድር በአዲስ አበባ ሲካሄድ የመጀመሪያው ሲሆን መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት የስፖርት መሰረተ ልማቶች መስፋፋት ምቹ ሆኔታ መፍጠሩ ነው የተገለፀው። በአዲስ አበባ ስታዲዮም በሚካሄደው ውድድር ላይ በዓለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ እና ብዙ ተከታይ ያላቸው አትሌቶች ይሳተፉበታል ተብሏል። ሲቲ ማውንቴን ባይክ ኢሊሚኔተር ዓለም አቀፍ የብስክሌት ውድድር እና ግራንድ ኢትዮጵያን ረን ሚያዝያ ውስጥ የሚካሄዱ ውድድሮች ናቸው። ከተማ አስተዳደሩ ውድድሩን ለማሳካት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቂ ዝግጅቶች ከማድረግ በዘለለ በኢትዮጵያ ያሉትን የስፖርት መሰረተ ልማቶች ለማስተዋወቅ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ ተመልክቷል።
ባየር ሙኒክ እና አርሰናል ለግማሽ ፍጻሜ አለፉ
Apr 16, 2026 264
አዲስን አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ቀሪ ሁለት የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በመደበኛው ክፍለ ጊዜ ባየር ሙኒክ ሪያል ማድሪድን 4 ለ 3 አሸንፏል። አሌክሳንደር ፓቭሎቪች፣ ሃሪ ኬን፣ሉዊስ ዲያዝ እና ማይክል ኦሊሴ ለባየር ሙኒክ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። አርዳ ጉለር ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኪሊያን ምባፔ ቀሪዋን ጎል ለማድሪድ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ተቀይሮ የገባው ኤድዋርዶ ካማቪንጋ በ86ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ወጥቷል። ከቀይ ካርዱ በኋላ ሙኒክ ሁለት ግቦችን አስቆጥሯል። በጨዋታው ባለሜዳው ባየር ሙኒክ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ሪያል ማድሪድ በመልሶ ማጥቃት የተሻሉ የግብ እድሎች ፈጥሯል። ከጨዋታው መጠናቀቅ በኋላ አርዳ ጉለር ዳኛ በመናገሩ በቀይ ካርድ ወጥቷል። ባየር ሙኒክ በድምር ውጤት 6 ለ 4 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። በሌላኛው መርሐ ግብር አርሰናል እና ስፖርቲንግ ሊዝበን ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በቂ የግብ እድሎች የተፈጠሩበት አልነበረም። ውጤቱን ተከትሎ አርሰናል በድምር ውጤት 1 ለ ዐ በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ተጠናቋል። በግማሽ ፍጻሜው ባየር ሙኒክ ከፒኤስጂ የሚያደርጉት ጨዋታ ከወዲሁ በጉጉት ይጠበቃል። አርሰናል በግማሽ ፍጻሜው ከአትሌቲኮ ማድሪድ ጋር ይገናኛል። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሚያዚያ ወር መጨረሻ ይደረጋሉ።
መቻል ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Apr 15, 2026 133
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መቻል ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ፤ መሐመድ ኑር ናስር በስድስተኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ድሬዳዋ መሪ ሆኗል። ዓለምብርሃን ይግዛው በ15ኛው እና ጋናዊው ኮሊንስ ኮፊ በ40ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፏቸው ግቦች መቻልን አሸናፊ አድርገዋል። የመቻሉ አማካይ ተጫዋች አብዱልከሪም ወርቁ በመጀመሪያው አጋማሽ ቡድኑ ያገኘውን የፍጹም ቅጣት ምት ሳይጠቀምበት ቀርቷል። በሊጉ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው መቻል በ43 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ32 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን እና ባህር ዳር ከተማ አንድ አቻ ሲለያዩ፤ ሐዋሳ ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ያካሄዱት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 27ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የ28ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከሚያዝያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም አጀምሮ ይካሄዳል።
ሀላባ ከተማ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አደገ
Apr 15, 2026 230
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የ2018 የውድድር ዘመን ምድብ ለ 20ኛ ሳምንት ወሳኝ ጨዋታ ዛሬ በሀላባ ከተማ እና ደሴ ከተማ መካከል ሀዋሳ ላይ ተካሂዷል። በጨዋታውም ሀላባ ከተማ ደሴ ከተማን 1 ለ 0 በማሸነፍ ነጥቡን 38 አድርሷል። ይህም አንድ ጨዋታ እየቀረው በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ 2019 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ማደጉን እንዲያረጋግጥ ማስቻሉን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የ2018 የውድድር ዘመን በምድብ ሀ መሪ ሆኖ ያጠናቀቀው ጋሞ ጨንቻ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ማደጉ ይታወቃል። የፌዴሬሽኑ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ ሁለት ክለቦች ወደ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሲያድጉ አራት ክለቦች ደግሞ ከሊጉ የሚወርዱ ይሆናል።
ሃዋሳ ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ነጥብ ተጋሩ
Apr 15, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት ሃዋሳ ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተደርጓል። ውጤቱን ተከትሎ ሃዋሳ ከተማ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከአራተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። ቡድኑ ባለፉት አራት የሊጉ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥሏል። ምድረ ገነት ሽሬ በ29 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ወደ 17ኛ ከፍ ቢያደርግም አሁንም ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን እና ባህር ዳር ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። አማኑኤል ኤርቦ በ41ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ግብ መድን መሪ ሆኗል። አደም አባስ በ96ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ለባህር ዳር ከተማ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን በ30 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ባህር ዳር ከተማ በ36 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በርካታ ጊዜ (በ15 ጨዋታዎች ) አቻ የወጣ ቡድን ነው።
በዓለም አትሌቲክስ ግራንድ ፕሪ የሚሳተፉ አትሌቶች በአዲስ አበባ ስታዲየም ልምምድ ጀመሩ
Apr 15, 2026 138
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7 /2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም አትሌቲክስ አዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአንድ ቀን ውድድር ተሳታፊ አትሌቶች በአዲስ አበባ ስታዲየም ዛሬ ልምምድ ማድረግ ጀምረዋል። የአዲስ አበባ ስታዲየም ከስምንት ዓመት በኋላ የመሮጫ ትራክ እድሳቱ ተጠናቅቆ ዛሬ በአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ ዓለም አቀፍ ውድድር ለሚሳተፉ አትሌቶች ክፍት ሆኗል። ባለፉት ዓመታት በእድሳት ምክንያት ከአገልግሎት ውጪ የነበረው ስታዲየሙ፣ በአዲስ መልክ እድሳት ተደርጎለት አሁን ለውድድርና ለልምምድ ዝግጁ መሆኑን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ቅዳሜ ሚያዚያ 10 የሚደረገውን የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአንድ ቀን ውድድር ስኬታማ እንዲሆን፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የመሮጫ መም እድሳቱን በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጠናቀቅ ላደረገው ርብርብ ፌዴሬሽኑ ምስጋናውን አቅርቧል። ሚኒስቴሩ ለኢትዮጵያ አትሌቲክስ እድገትና ልማት የሰጠው ልዩ ትኩረት ለስፖርቱ መነቃቃት የማይተካ ሚና እንዳለው በመረጃው ላይ ተመላክቷል። የዓለም አትሌቲክስ ዓመታዊ አህጉራዊ ውድድር አካል የሆነው አዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአንድ ቀን ውድድር በኢትዮጵያ ሲካሄድ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።
ሃዋሳ ከተማ ከምድረ ገነት ሽሬ መቻል ከድሬዳዋ ከተማ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ዛሬ ይጠበቃሉ
Apr 15, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ሃዋሳ ከተማ ከምድረ ገነት ሽሬ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሃዋሳ ከተማ በውድድር ዓመቱ 26 ጨዋታዎችን አድርጎ በ11ዱ ሲያሸንፍ በሰባቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ስምንት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። 30 ግቦችን በ26ቱ ጨዋታዎች ላይ ሲያስቆጥር 21 ጎሎችን አስተናግዷል። ሃዋሳ ከተማ በ41 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ካከናወናቸው 26 ጨዋታዎች መካከል ስድስቱን ያሸነፈው ምድረ ገነት ሽሬ በበኩሉ 10 ጊዜ ተሸንፏል። 10 ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 17 ግቦችን ሲያገባ 21 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ምድረ ገነት ሽሬ በ28 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ባለፉት ሶስት የሊጉ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ ማሸነፍ በዋንጫ ፉክክሩ ለመቆየት የሚያስችለውን ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያገኛል። ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ ያደርጋል። ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች አንዱንም ማሸነፍ ያልቻለው ምድረ ገነት ሽሬ ሶስት ነጥብ ማግኘት ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ጥረት ወሳኝ የሚባል ነው። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በዝናብ ምክንያት ሳይካሄድ ቀርቶ ከሚያዚያ 5 ወደ ዛሬ የተሸጋገረ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ድሬዳዋ ከተማ ከመቻል በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ድሬዳዋ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው 26 ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ሲያሸንፍ ስምንት ጊዜ ተሸንፏል። 11 ጊዜ አቻ ተለያይቷል። 18 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያስቆጥር 25 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ32 ነጥብ 14ተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በበኩሉ በውድድር ዓመቱ 26 ጨዋታዎችን አድርጎ በ10ሩ ድል ሲቀናው ስድስት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ 10 ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። 33 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 21 ግቦች ተቆጥረውበታል። መቻል በ40 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ26ኛ ሳምንት ድሬዳዋ ከተማ ምድረ ገነት ሽሬን 1 ለ 0፣ መቻል የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡናን 3 ለ 1 አሸንፈዋል። ሁለቱም ቡድኖች በድል ጉዟቸው ለመቀጠል ይፋለማሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ መድን ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ መድን በሊጉ ባካሄዳቸው 26 ጨዋታዎች ስድስት ጊዜ ሲያሸንፍ ዘጠኝ ጊዜ ተሸንፏል። በ11 ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 20 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ በተመሳሳይ 20 ጎሎች ተቆጥረውበታል። መድን በ29 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ባህር ዳር ከተማ በበኩሉ ከ26 የሊጉ ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ሲያሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አጋጥሞታል። በ14 ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 19 ግቦች ሲያስቆጥር 18 ግቦችን አስተናግዷል። ባህር ዳር ከተማ በ35 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ድል ያልቀናው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ስጋት በመጠኑ እንዲርቅ ያስችለዋል። በ26ኛ ሳምንት አዳማ ከተማን 2 ለ 1 የረታው ባህር ዳር ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በርካታ ጊዜ (በ14 ጨዋታዎች ) አቻ የወጣ ቡድን ነው።
የባየር ሙኒክ እና የሪያል ማድሪድ ተጠባቂ የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታ
Apr 15, 2026 266
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ቀሪ ሁለት የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ዛሬ ማምሻውን ይካሄዳሉ። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ባየር ሙኒክ ከሪያል ማድሪድ 75 ሺህ 24 ተመልካቾችን በሚያስተናግደው አሊያንዝ አሬና ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ሁለቱ ቡድኖች ባለፈው ሳምንት በበርናባው ባካሄዱት ጨዋታ ባየር ሙኒክ 2 ለ 1 አሸንፏል። ሉዊስ ዲያዝ እና ሃሪ ኬን የማሸነፊያ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። ኪሊያን ምባፔ ለማድሪድ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱ ባየር ሙኒክ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ ያለውን እድል የተሻለ አድርጓል። የ15 ጊዜ የዋንጫው ባለቤት ሪያል ማድሪድ ወደ ግማሽ ፍጻሜ የመግባት እድሉ ያበቃለት አይደለም። በሻምፒዮንስ ሊጉ ላይ ትኩረቱን ያደረገው ማድሪድ ውጤቱን ለመቀልበስ ጠንካራውን ባየር ሙኒክ ማሸነፍ ይጠበቅበታል። የስድስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ባየር ሙኒክ፣ ወደ ግማሽ ፍፃሜው (አራት ውስጥ) የመግባት ዕድሉ በራሱ እጅ ላይ ይገኛል። በሌላኛው መርሐ ግብር አርሰናል ስፖርቲንግ ሊዝበንን ምሽት አራት ሰዓት ላይ በኤምሬትስ ስታዲየም ያስተናግዳል። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ጨዋታ አርሰናል ከሜዳው ውጪ በካይ ሃቫርትዝ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል። አርሰናል ወደ ግማሽ ፍጻሜ የመግባት ሰፊ ግምት አግኝቷል። የፖርቹጋሉ ስፖርቲንግ ሊዝበን ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ በውድድሩ ጠንካራ ቡድን የሆነውን አርሰናልን ከሜዳው ውጪ የማሸነፍ ከባድ የቤት ስራ ይጠብቀዋል። ትናንት በተደረጉ የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ፒኤስጂ ሊቨርፑልን፣ አትሌቲኮ ማድሪድ ባርሴሎናን በድምር ውጤት በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል።
ፒኤስጂ እና አትሌቲኮ ማድሪድ ለግማሽ ፍጻሜ አለፉ
Apr 15, 2026 205
አዲስን አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሁለት የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፒኤስጂ ሊቨርፑልን 2 ለ 0 አሸንፏል። ኡስማን ዴምቤሌ በ72ኛው እና 91ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎሎቹን አስቆጥሯል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ በድምር ውጤት 4 ለ 0 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። ፒኤስጂ በግማሽ ፍጻሜው ከባየር ሙኒክ እና ሪያል ማድሪድ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ባርሴሎና አትሌቲኮ ማድሪድን 2 ለ 1 አሸንፏል። በዋንዳ ሜትሮፖሊታኖ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ላሚን ያማል እና ፌራን ቶሬስ ለባርሴሎና ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አዴሞላ ሉክማን ለአትሌቲኮ ማድሪድ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። የባርሴሎናው ኤሪክ ጋርሺያ በ80ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በመጀመሪያው ጨዋታም የባርሴሎናው ፓው ኩባርሲ በቀይ ካርድ መውጣቱ የሚታወስ ነው። በጨዋታው ባርሴሎና ብልጫ ቢወስድም ጨዋታውን ለመቀልበስ የሚያስችሉ ተጨማሪ ጎሎችን ማስቆጠር አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ አትሌቲኮ ማድሪድ በድምር ውጤት 3 ለ 2 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። የማድሪዱ ክለብ በግማሽ ፍጻሜው ከአርሰናል እና ስፖርቲንግ ሊዝበን አሸናፊ ጋር ይጫወታል። የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ነገም ሲቀጥል ባየር ሙኒክ ከሪያል ማድሪድ እና አርሰናል ከስፖርቲንግ ሊዝበን ይጫወታሉ።
ፋሲል ከነማ ደረጃውን ወደ ሶስተኛ ከፍ አደረገ
Apr 14, 2026 282
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ፋሲል ከነማ ወላይታ ድቻን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ታምራት እያሱ በ20ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ታምራት በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ዘጠኝ አድርሷል። ውጤቱን ተከትሎ በሊጉ 10ኛ ድሉን ያስመዘገበው ፋሲል ከነማ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ወላይታ ድቻ በ31 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ27ኛ ሳምንት ጨዋታዎች የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ አዳማ ከተማን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ሀድያ ሆሳዕና እና ኢትዮጵያ ቡና ሁለት አቻ ተለያይተዋል።