ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የዓለም ዋንጫ ተስፋን ለማለምለም የሚደረግ ፍልሚያ፤ ቀይ ቀበሮዎች ከካርቴጅ ንስሮች
May 19, 2026 14
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ የመጨረሻ ጨዋታዋን ዛሬ ከቱኒዚያ ጋር ታከናውናለች። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ አካዳሚ ይካሄዳል። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በምድብ አንድ ባደረጋቸው ሁለት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲሸነፍ በቀሪው መርሐ ግብር አቻ ተለያይቷል። ከግብጽ ጋር ያለ ግብ አቻ ሲለያይ በአዘጋጇ ሞሮኮ 2 ለ 1 ተሸንፏል። ብሔራዊ ቡድን በአንድ ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ከሞሮኮ ጋር በነበረው ጨዋታ የተሻለ እንቅስቃሴ አድርጓል። ተጋጣሚዋ ቱኒዚያ ከሁለት ጨዋታዎች አንድ ነጥብ በማግኘት ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ዓለም ዋንጫ የማለፍ ህልሟን ለማለምለም የግድ ቱኒዚያን ማሸነፍ ይጠበቅበታል። ቀይ ቀበሮቹ ሁለተኛ ደረጃን ይዘው ካጠናቀቁ ቀጥታ በኳታር ለሚካሄደው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በቀጥታ ያልፋሉ። በአንጻሩ ሶስተኛ ከወጡ ወደ ዓለም ዋንጫ ለማለፍ ወደ ሚደረገው ማጣሪያ ይሸጋገራሉ። አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር ከጨዋታው በፊት በሰጡት አስተያየት አላማቸውን ለዓለም ዋንጫ ማለፍ መሆኑን ተናግረዋል። ለዚህም እየሰራን ነው ሲሉ ገልጸዋል። ብሔራዊ ቡድኑ እስከ መጨረሻው እንደሚፋለም እና ቱኒዚያን ለማሸነፍ እንደሚጫወት ተናግረዋል። ቡድኑ ከጨዋታው በፊት የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት በመሐመድ ስድስተኛ አካዳሚ ማከናወኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በዚሁ ምድብ በተመሳሳይ ከምሽቱ አራት ሰዓት አዘጋጇ ሞሮኮ ከግብጽ ጋር ትጫወታለች። ሞሮኮ እና ግብጽ በተመሳሳይ አራት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ይዘዋል። ጨዋታው በአቻ ውጤት ከተጠናቀቀ ሁለቱ ሀገራት በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ማለፋቸውን ያረጋግጣሉ። ጨዋታውን የሚያሸንፈው ቡድን ለዓለም ዋንጫ ከማለፍ ባለፈ ምድቡን በመሪነት ያጠናቅቃል። ሽንፈት የሚያስተናግደው ብሔራዊ ቡድን በሂሳባዊ ስሌት ወደ ዓለም ዋንጫው የመግባት እድል አለው። 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ እስከ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በአፍሪካ ዋንጫው ከሚሳተፉ 16 ሀገራት መካከል የተሻለ ውጤት የሚያስመዘግቡ 10 ሀገራት በጥቅምት እና ህዳር ወር 2019 ዓ.ም በኳታር ለሚካሄደው 20ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ያልፋሉ። በዓለም ዋንጫው 48 ሀገራት ይሳተፋሉ።
መቻል የሊጉን መሪነት ከሲዳማ ቡና መረከብ የሚያስችለውን ጨዋታ ከባህር ዳር ከተማ ጋር ያደርጋል
May 19, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ዛሬ በሚደረጉ ሶስት ጨዋታዎች ይጀመራል። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ባህር ዳር ከተማ ከመቻል በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ባህር ዳር ከተማ በ47 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በ52 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ32ኛ ሳምንት ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 ያሸነፈው ባህር ዳር ከተማ በድል ጉዞው ለመቀጠል ይፋለማል። በተመሳሳይ በ32ኛ ሳምንት ነገሌ አርሲን 4 ለ 0 የረታው መቻል ካሸነፈ ከሲዳማ ቡና በነጥብ እኩል በመሆን በግብ ክፍያ ብልጫ መሪነቱን ይረከባል። ይህም በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ የሚባል ምዕራፍ ይከፍታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ መድን ከወላይታ ድቻ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን በ41 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ወላይታ ድቻ በ42 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። በ32ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ መድን ከመቀሌ 70 እንደርታ አንድ አቻ ሲለያይ ወላይታ ድቻ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ያደረገው ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታው ለሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ከመመለስ ባለፈ በወራጅ ቀጠና ስፍራ ከሚገኙ ክለቦች በነጥብ ለመራቅ ያስችላቸዋል። ሀዲያ ሆሳዕና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ባለፉት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ያሸነፈው ሀዲያ ሆሳዕና በ41 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተመሳሳይ 41 ነጥብ በግብ ክፍያ ብልጫ ወስዶ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ32ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሸገር ከተማን 2 ለ 1 ረቷል። ሁለቱም ቡድኖች በድል ጉዟቸው ለመዝለቅ የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት እስከ ግንቦት 13 ቀን 2013 ዓ.ም ይቆያል። ሲዳማ ቡና በ55 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን አቤል ያለው ከሲዳማ ቡና በ14 ጎሎች እየመራ ነው። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኮቹ ናትናኤል ዳንኤል እና አዲስ ግደይ፣ የፋሲል ከነማው ታምራት ኢያሱ በተመሳሳይ 11 ግቦች ይከተላሉ።
ማንችስተር ሲቲ በዋንጫ ፉክክሩ የመቆየት ህልሙን ለማስቀጠል ከቦርንማውዝ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው
May 19, 2026 119
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት ዛሬ በሚደረጉ ጨዋታዎች ፍጻሜውን ያገኛል። ምሽት 3 ሰዓት ከ30 ላይ ቦርንማውዝ ከማንችስተር ሲቲ የሚያደርጉት ጨዋታ የብዙዎችን ትኩረት ስቧል። ቦርንማውዝ በ55 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ በ77 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቦርንማውዝ ባለፉት 16 የሊግ ግጥሚያዎች ሽንፈትን ሳያስተናግድ በአስደናቂ ግስጋሴ ላይ ይገኛል። ማንችስተር ሲቲ በዋንጫው ፉክክር ለመቆየት እና የሊጉን አሸናፊ በመጨረሻው ሳምንት እንዲወሰን ለማድረግ ከዛሬው ጨዋታ ሶስት ነጥብ መውሰድ ግድ ይለዋል። ሲቲ ካሸነፈ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ ያደርጋል። ሻምፒዮንስ ሊግ የመግባት ተስፋ ያለው ቦርንማውዝ ለማንችስተር ሲቲ ጠንካራ ተፋላሚ እንደሚሆን ይጠበቃል። በሌላኛው መርሐ ግብር ቼልሲ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ ምሽት 4 ሰዓት ከ15 ላይ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቼልሲ በ49 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ38 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በሊጉ የዓመቱን የመጨረሻ የሜዳ ጨዋታውን የሚያደርገው ቼልሲ ከሰባት የሊግ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከጨዋታው አንድ ነጥብ ካገኘ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል። በወራጅ ቀጠና የሚገኘው ዌስትሃም ዩናይትድ ትናንት በኒውካስትል ዩናይትድ 3 ለ 1 መሸነፉን ተከትሎ ስፐርስ በሊጉ የመቆየቱ እድል ይበልጥ ሰፍቷል።
አርሰናል የሊጉን ዋንጫ ለማንሳት ይበልጥ የተቃረበበትን ወሳኝ ድል አስመዘገበ
May 18, 2026 303
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር አርሰናል በርንሌይን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ካይ ሃቫርትዝ በ36ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎል አስቆጥሯል። አርሰናል በሊጉ ከማዕዘን ምት ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት 24 አድርሷል። ባለሜዳው አርሰናል የተሻለ እንቅስቃሴ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 25ኛ ድሉን ያስመዘገበው የሊጉ መሪ አርሰናል በ82 ነጥብ ወደ ዋንጫው ይበልጥ የቀረበበትን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ አድርጓል። ተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ነገ ከቦርንማውዝ ከሜዳው ውጪ የሚያደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ማንችስተር ሲቲ ነጥብ ከጣለ አርሰናል የሊጉ አሸናፊ መሆኑን ያረጋግጣል። በአንጻሩ በሊጉ 24ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው በርንሌይ በ21 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዟል። በርንሌይ ከሊጉ መውረዱ ይታወቃል።
የሊጉ መሪ አርሰናል ከበርንሌይ ጋር ይጫወታል
May 18, 2026 393
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት አርሰናል ከበርንሌይ ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሁለቱ ክለቦች መርሐ ግብር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በኤምሬትስ ስታዲየም ይካሄዳል። አርሰናል በ79 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ካሸነፈ ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ ያደርጋል። ጨዋታው ለመድፈኞቹ ዋንጫውን ለማንሳት እያደረጉት ባለው ጉዞ እጅጉን ወሳኝ የሚባል ነው። የሰሜን ለንደኑ ክለብ የዋንጫውን ዕድል ራሱ የመወሰን ዕድል አለው። ከሊጉ መውረዱ የተረጋገጠው በርንሌይ በ21 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዟል። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ጨዋታ አርሰናል 2 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። የ45 ዓመቱ ፖል ቲርኒ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና 15 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ውድድሩን በሶስተኝነት አጠናቀቀች
May 18, 2026 223
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ ከግንቦት 5 አንስቶ ሲካሄድ የቆየው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ማምሻውን ተጠናቋል። ኢትዮጵያ በአምስት ወርቅ፣ አራት የብር እና ስድስት የነሐስ በአጠቃላይ 15 ሜዳሊያዎችን በመሰብሰብ ውድድሩን ሶስተኛ በመሆን አጠናቃለች። በአህጉራዊው መድረክ ላይ ኢትዮጵያን ወክለው የገቡ አትሌቶች ባስመዘገቡት አንጸባራቂ ድል በኩራት የኢትዮጵያን ባንዲራ ከፍ ማድረግ መቻላቸውን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በውድድሩ ከፍተኛውን ክብር ያገኙትና የወርቅ ሜዳሊያ ያሸነፉት አትሌቶች አትሌት አጃይባ አልዩ ፣ አትሌት ምስጋና ኃይሉ፣ አትሌት ገመቹ ጎዳና ፣አትሌት ምስጋናው ዋቁማ እና አትሌት ውብአለም ሽጉጤ ናቸው። የብር ሜዳሊያ ስኬት ያስመዘገቡት አትሌቶችና ቡድኖች ደግሞ የ4 በ 400 ሜትር የሴቶች ሪሌ ቡድን፣ አትሌት ኦታጌ ኦባንግ፣ አትሌት ሙቢን ሀጂ እና አትሌት ሀጎስ እዮብ መሆናቸው ታውቋል። በውድድሩ የነሐስና የክብር አሻራቸውን ያሳረፉት ቀሪዎቹ ስኬታማ አትሌቶች ደግሞ አትሌት አልማዝ ዮሐንስ፣ አትሌት ሳሙኤል ፍሬው፣ አትሌት ዘይን አየልኝ፣ አትሌት በፀሎት አለማየሁ፣ አትሌት አሰፉ አብርሃ እና አትሌት አብዱልሰላም አብዱልዋሂብ ናቸው። ኢትዮጵያ በዚህ በአህጉሪቱ የስፖርት መድረክ ላይ በ32 ሴት እና በ31 ወንድ አትሌቶች፣ በአጠቃላይ 63 አባላትን በመያዝ ጠንካራ ተሳትፎ አድርጋለች። የተመዘገበው ስኬት የኢትዮጵያን የአትሌቲክስ የበላይነት በአህጉሪቱ መድረክ ላይ ዳግም ያስመሰከረ መሆኑን ፌዴሬሽኑ አመልክቷል። ኬንያ ስድስት የወርቅ፣ አራት የብር እና ሰባት የነሐስ በድምሩ 17 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ውድድሩን በአንደኝነት አጠናቃለች። ደቡብ አፍሪካ በስድስት የወርቅ፣ ሁለት የብር እና ስድስት የነሐስ በድምሩ 12 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። ናይጄሪያ እና ኮትዲቭዋር አራተኛና አምስተኛ ደረጃን ይዘዋል። በሻምፒዮናው ላይ ከተሳተፉ ሀገራት መካከል 25ቱ የሜዳሊያ ሰንጠረዥ ውስጥ ገብተዋል። ኢትዮጵያ በካሜሮን ዱዋላ በተደረገው 23ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአምስት የወርቅ፣ አራት የብር እና አንድ የነሃስ በድምሩ 10 ሜዳሊያዎችን በማግኘት አራተኛ መውጣቷ የሚታወስ ነው። ኢትዮጵያ በዘንድሮው ሻምፒዮና የሜዳሊያ ብዛት እና ደረጃዋን አሻሽላለች።
በወራጅ ቀጠና የሚገኘው ዌስትሃም ዩናይትድ በኒውካስትል ዩናይትድ ተሸነፈ
May 17, 2026 392
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኒውካስትል ዩናይትድ ዌስትሃም ዩናይትድን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዊሊያም ኦሱላ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኒክ ዎልትማደ ቀሪዋን ጎል ለኒውካስትል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቫለንቲን ካስቴላኖስ ለዌስትሃም የማስተዛዘኛውን ጎል አስቆጥሯል። ባለሜዳው ኒውካስትል ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። በሊጉ 14ኛ ድሉን ያስመዘገበው ኒውካስትል ዩናይትድ በ49 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 19ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ዌስትሃም ዩናይትድ በ36 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የለንደኑ ክለብ በሊጉ የመቆየት ተስፋው ተመናምኗል። ማክሰኞ ቶተንሃም ቼልሲን ካሸነፈ ዌስትሃም ወደ ሻምፒዮንሺፑ ይወርዳል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ ኖቲንግሃም ፎረስትን 3 ለ 2 በማሸነፍ በ68 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ መጨረሱን አረጋግጧል። ሰንደርላንድ ኤቨርተንን 3 ለ 1፣ ሊድስ ዩናይትድ ብራይተንን 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ብሬንትፎርድ ከክሪስታል ፓላስ ሁለት አቻ ሲለያዩ ፉልሃም እና ዎልቭስ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። የ37ኛ ሳምንት ነገም ቀጥሎ ሲውል የሊጉ መሪ አርሰናል ከበርንሌይ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ከነገ በስቲያ ቦርንማውዝ ከማንችስተር ሲቲ እና ቼልሲ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለ6ኛ ተከታታይ ዓመት የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አሸናፊ ሆነ
May 17, 2026 243
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የውድድር ዓመቱ የመጨረሻ ጨዋታ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ መካከል ተከናውኗል። በዚህም መሠረት፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በእሙሽ ዳንኤል እና ረድዔት አስረሳኸኝ ግቦች ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 0 አሸንፏል። ውጤቱን ተከትሎም፤ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለ6ኛ ተከታታይ ዓመት በአጠቃላይ ለ9ኛ ጊዜ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አሸናፊ ሆኗል። ቀደም ብሎ በተከናወነ የዕለቱ መርሐ-ግብር መቻል እና አዲስ አበባ ከተማ 2 አቻ ተለያይተዋል። ይህን ተከትሎም መቻል በ56 ነጥብ 3ኛ ደረጃን ይዞ የውድድር ዓመቱን ሲያጠናቅቅ፤ በ16 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀው አዲስ አበባ ከተማ ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ ወርዷል።
ማንችስተር ዩናይትድ ኖቲንግሃም ፎረስትን አሸነፈ
May 17, 2026 173
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፡- በ37ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ኖቲንግሃም ፎረስትን በኦልድትራፎድ ያስተናገደው ማንችስተር ዩናይትድ 3 ለ 2 ረትቷል። የማንችስተር ዩናይትድን ግቦች፤ በ5ኛው ደቂቃ ሉክ ሾው፣ ማቲውስ ኩንያ በ54ኛው ደቂቃ እንዲሁም ምቤሞ በ75ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የኖቲንግሃም ፎረስትን ግቦች ደግሞ፤ በ52ኛው ደቂቃ ሞራቶ በ77ኛው ደቂቃ ጊብስ ዋይት አስቆጥረዋል። የጨዋታውን ውጤት ተከትሎም ማንችስተር ዩናይትድ በ68 ነጥብ ባለበት 3ኛ ደረጃ ላይ ሲሆን፤ ኖቲንግሃም ፎረስት በ43 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ፖርቹጋላዊው አማካይ ብሩኖ ፈርናንዴዝ በውድድር ዓመቱ 20 ለግብ የሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል፤ በቴሪ ሄንሪ እና ኬቨን ዴብሮይን ተይዞ የነበረውን በአንድ ዓመት ብዙ ጎል አመቻችቶ የማቀበል ክብረ ወሰን ተጋርቷል። የዕለቱ የጨዋታ መርሐ-ግብሮች ሲቀጥሉ፤ በተመሳሳይ 11 ሠዓት ላይ ብሬንትፎርድ ከፓላስ፣ ሊድስ ከብራይተን፣ ዎልቭስ ከፉልሃም፣ ኤቨርተን ከሰንደርላንድ የሚጫወቱ ይሆናል። በሌላ በኩል ኒውካስትል ከዌስትሃም ምሽት 1 ሠዓት ከ30 ላይ እንደሚጫወቱ የወጣው መርሐ-ግብር ያስረዳል፡፡
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ መቻል እና አዲስ አበባ ከተማ ነጥብ ተጋሩ
May 17, 2026 167
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት መቻል እና አዲስ አበባ ከተማ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ትንቢት ሳሙኤል በጨዋታ እና ትዕግስት ወርቁ በፍጹም ቅጣት ምት ለመቻል ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዓለምነሽ ገረመው ለአዲስ አበባ ከተማ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ሁለት ግቦች ያስቆጠረችው ዓለምነሽ ገረመው የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። መቻል በ56 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ የውድድር ዓመቱን አጠናቋል። ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ የወረደው አዲስ አበባ ከተማ በ16 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ዋንጫውን ለማንሳት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል።
የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የመጨረሻ ቀን ውሎ
May 17, 2026 198
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ይጠናቀቃል። ሻምፒዮናው ከግንቦት 5 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በጋና ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ሲካሄድ ቆይቷል። በውድድሩ መዝጊያ ቀን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉባቸው የፍጻሜ ውድድሮች ይካሄዳሉ። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው አምስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና አምስት የነሐስ በድምሩ 11 ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በሻምፒዮናው ላይ ኢትዮጵያ 31 ሴቶች እና 32 ወንዶች በድምሩ 63 አትሌቶችን አሳትፋለች። በውድድሩ ላይ ከ54 ሀገራት የተወጣጡ አትሌቶች ተሳታፊ ሆነዋል።
ዋንጫውን ማን ያነሳል? ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ?
May 17, 2026 185
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል። ጨዋታው ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባደረጋቸው 25 ጨዋታዎች 21 ድሎችን ሲቀዳጅ የተሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 71 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ስምንት ጎሎችን ብቻ አስተናግዷል። ንግድ ባንክ በ66 ነጥብ ሊጉን እየመራ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ በርካታ ግቦችን ያስቆጠረ እና አነስተኛ የጎል መጠን ያስተናገደ ቡድን ነው። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በውድድር ዘመኑ 25 ጨዋታዎችን አከናውኖ በ21ዱ ሲያሸንፍ በአንድ ጨዋታ ብቻ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። በ24ቱ ጨዋታዎች ላይ 52 ግቦችን ሲያስቆጥር 12 ጎሎችን ተቆጥረውበታል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በተመሳሳይ 66 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 63 እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ 41 የግብ ክፍያ አላቸው። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ ለስድስተኛ ተከታታይ የውድድር ዓመት ዋንጫውን ያነሳል። በአጠቃላይ ለዘጠነኛ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ይሆናል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሊጉን ለማሸነፍ የግድ ጨዋታውን ማሸነፍ ይኖርበታል። ቡድኑ ካሸነፈ ለመጀመሪያ ጊዜ የፕሪሚየር ሊጉን ዋንጫ ያነሳል። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በ24 ግቦች ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የምትመራው የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን፣ በ20 ግቦች የምትከተለው የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ በጨዋታው ትኩረት ያገኙ ተጫዋቾች ናቸው። ሁለቱ ቡድኖች በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ተገናኝተው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን በማህሌት ምትኩ ጎል 1 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር መቻል ከአዲስ አበባ ከተማ ከረፋዱ አምስት ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቻል በ55 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ መውረዱ የተረጋገጠው አዲስ አበባ ከተማ በ15 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የመጨረሻ ሳምንት የሆነው የ26ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከ25ኛ ሳምንት በፊት አስቀድሞ ተደርጓል። የመርሐ ግብሩ ቅያሬ ከዋንጫ ተፎካካሪዎቹ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር የተገናኘ መሆኑ ተገልጿል። የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ፍጻሜውን ያገኛል።
ማንችስተር ዩናይትድ ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር ይጫወታል
May 17, 2026 155
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 37ኛ ሳምንት ዛሬ ስድስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ 8 ሰዓት ከ30 ላይ ማንችስተር ዩናይትድ ኖቲንግሃም ፎረስትን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም ያስተናግዳል። የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን ያረጋገጠው ማንችስተር ዩናይትድ በ65 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኖቲንግሃም ፎረስት በ43 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ዩናይትድ ካሸነፈ በሊጉ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁን ያረጋግጣል። ጨዋታው ጊዜያዊው አሰልጣኝ ማይክል ካሪክ በክለቡ በቋሚነት የሚቀጥልበት የሁለት ዓመት ውል በተፈራረመ ማግስት የሚደረግ መሆኑ ትኩረትን ስቧል። በፕሪሚየር ሊጉ መቆየቱን ያረጋገጠው ኖቲንግሃም ፎረስት ከ36ኛ ሳምንት የአቻ ውጤት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኒውካስትል ዩናይትድ ከዌስትሃም ዩናይትድ ምሽት 1 ሰዓት ከ30 በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኒውካስትል ዩናይትድ በ46 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ36 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የመውረድ አጣብቂኝ ውስጥ የገባው ዌስትሃም ዩናይት ካሸነፈ በጊዜያዊነት ከወራጅነት ቀጠና በመውጣት ቶተንሃም ሆትስፐርስ ላይ ጫና ያሳድራል። በ36ኛ ሳምንት ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር አንድ አቻ የተለያየው ኒውካስትል ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። ብሬንትፎርድ ከክሪስታል ፓላስ፣ ሊድስ ዩናይትድ ከብራይተን፣ ዎልቭስ ከፉልሃም እና ኤቨርተን ከሰንደርላንድ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በአዘጋጇ ሞሮኮ ተሸነፈ
May 16, 2026 331
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አንድ መርሐ ግብር ሞሮኮ ኢትዮጵያን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ማምሻውን በመሐመድ ስድስተኛ ስፖርት አካዳሚ በተካሄደው ጨዋታ ዳዊት ካሳው በ24ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ኢትዮጵያ መሪ ሆናለች። ከእረፍት መልስ በ47ኛው ደቂቃ መሐመድ ሙስታሽ ሞሮኮን አቻ ያደረገችውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ ተብሎ ሲጠበቅ ኢምራን ታላይ በ91ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ሞሮኮን አሸናፊ አድርጓል። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በጨዋታው ጥሩ የማጥቃት እንቅስቃሴ ያደረገ ሲሆን ተጨማሪ ግቦችን ማስቆጠር የሚችልባቸውን እድሎች መጠቀም አልቻለም። ብሔራዊ ቡድኑ ውጤቱን ተከትሎ በአንድ ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በመጀመሪያ ጨዋታው ከግብጽ ጋር አቻ መውጣቱ ይታወቃል። አዘጋጇ ሞሮኮ በአራት ነጥብ ምድብ አንድን እየመራች ነው። ሞሮኮ የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ናት። ዛሬ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ግብጽ ቱኒዚያን በማሸነፍ በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በአሜሪካዊው ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው ብሔራዊ ቡድን የመጨረሻ የምድብ ጨዋታውን ማክሰኞ ግንቦት 11 ቀን 2018 ዓ.ም ከቱኒዚያ ጋር ያደርጋል። ቡድኑ በኳታር ለሚካሄደው የዓለም ዋንጫ የማለፍ ተስፋውን ለማለምለም ሶስት ነጥብ ማግኘት ግድ ይለዋል። ሞሮኮ ከግብጽ ሌላኛው የሚደረግ የመጨረሻ የምድብ ጨዋታ ነው።
ፋሲል ከነማ ወደ ድል ተመልሷል
May 16, 2026 245
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ፋሲል ከነማ አዳማ ከተማን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ታምራት ኢያሱ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ቃልኪዳን ዘላለም ቀሪዋን ጎል ለፋሲል ከነማ ከመረብ ላይ አሳርፏል። የፋሲል ከነማው አብዱልአዚዝ አማን በራሱ መረብ ላይ ያስቆጠረው ጎል ለአዳማ ከተማ ብቸኛ ግብ ሆኖ ተመዝግቧል። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ፋሲል ከነማ በ46 ነጥብ ደረጃውን ከስምንተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉም 11ኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ38 ነጥብ በበኩሉ ከነበረበት 15ኛ ደረጃ ወደ 16ኛ ዝቅ ብሏል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ የ32ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 ሲያሸንፍ ሃዋሳ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የጨዋታዎቹን መጠናቀቅ ተከትሎ 32ኛ ሳምንት ፍጻሜውን አግኝቷል። የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከግንቦት 11 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳል።
ማንችስተር ሲቲ ለስምንተኛ ጊዜ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን አነሳ
May 16, 2026 235
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኤፍኤ ካፕ የፍጻሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ቼልሲን 1 ለ 0 አሸንፏል። በዌምብሌይ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶዋን ሴሜኒዮ በ71ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሴሜኒዮ የግል ድንቅ ብቃቱን ተጠቅሙ በተለምዶ ‘ቄንጠኛ’ በሚባል መልኩ ያስቆጠራት ጎል አስደማሚ የሚባል ነው። ማንችስተር ሲቲ በተጋጣሚው ላይ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። ድሉን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ የኤፍኤ ካፑን ዋንጫ ለስምንት ጊዜ አንስቷል። ውሃ ሰማያዊዎቹ ከሶስት ዓመታት በኋላ አንጋፋውን ውድድር አሸንፈዋል። ሲቲ ከካራባኦ ካፕ በኋላ በዘንድሮው የውድደር ዓመት ሁለተኛ ዋንጫውን አገኝቷል። በአንጻሩ ቼልሲ ለዘጠነኛ ጊዜ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን የማንሳት ህልሙ አልተሳካም። ሰማያዊዎቹ ለመጨረሻ ጊዜ ውድድሩን ያሸነፈው እ.አ.አ 2018 ነው። ቼልሲ ዋንጫውን ቢያነሳ ዩሮፓ ሊግ የመግባት እድል ያገኝ ነበር።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒርሲቲ ድል ሲቀናው ሃዋሳ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ አቻ ተለያይተዋል
May 16, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መካሄዱን ቀጥሏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። ጋናዊው ኮንኮኒ ሃፊዝ እና እንዳልካቸው ጥበቡ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አቤል ሀብታሙ የኢትዮ ኤሌክትሪክን ብቸኛ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ39 ነጥብ ደረጃውን ከ16ኛ ወደ 15ኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉም ዘጠነኛ ድሉን አሳክቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ45 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው መርሐ ግብር ሃዋሳ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ሃዋሳ ከተማ በ45 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ዘጠኝ የሊጉ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ በውጤት ማጣት ቀውስ ይገኛል። አርባምንጭ ከተማ በ29 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሲሆን ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም።
ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ መቆየቱን ሲያረጋግጥ አዲስ አበባ ከተማ ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ ወርዷል
May 16, 2026 157
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ሸገር ከተማ እና ይርጋጨፌ ቡና ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተካሄዷል። የይርጋጨፌ ቡናዋ ግብ ጠባቂ የኔነሽ አበበ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ይርጋጨፌ ቡና በ19 12ኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ በሊጉ መቆየቱን አረጋግጧል። በአንጻሩ በ15 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አዲስ አበባ ከተማ ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ ወርዷል። አርባምንጭ ከተማ አስቀድሞ ወደ ከፍተኛ ሊግ መውረዱ ይታወቃል። ሸገር ከተማ በበኩሉ በ48 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን በመያዝ የውድድር ዓመቱን አጠናቋል። በሌላኛው መርሐ ግብር ድሬዳዋ ከተማ አዳማ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ድሬዳዋ ከተማ ድል ቀንቶታል
May 16, 2026 116
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ድሬዳዋ ከተማ አዳማ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ዝናሽ ሰለሞን እና ፊርማዬ ከበደ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አህላም ሲራጅ የአዳማ ከተማን ብቸኛ ጎል አስቆጥራለች። የድሬዳዋ ከተማዋ አምበል ሊና መሐመድ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ ስምንተኛ ድሉን ያስመዘገበው ድሬዳዋ ከተማ በ28 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዞ የውድድር ዓመቱን አጠናቋል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 14ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በበኩሉ በ22 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል።
ኢትዮጵያ በ20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር በሁለቱም ጾታዎች የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 16, 2026 168
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛ የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ አምስተኛ ቀኑን ይዟል። በወንዶች 20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር አትሌት ምስጋናው ዋቁማ አሸንፏል። ውድድሩን በአንደኝነት በማጠናቀቅ በአፍሪካ ሻምፒዮና መድረክ በተከታታይ ለሁለተኛ ጊዜ በማሸነፍ ክብሩን አስጠብቋል። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት አብዱልሰላም አብዱልዋሂብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ የነሐስ ሜዳሊያ ለሀገሩ አስገኝቷል። በሴቶች 20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር ደግሞ አትሌት ውብአለም ሽጉጤ በቀዳሚነት አጠናቃ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። በዚሁ ውድድር ላይ የተካፈሉት አትሌት ሕይወት አምባው አራተኛ እንዲሁም አትሌት ማሬ ቢተው ስምንተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድራቸውን አጠናቀዋል። ውጤቶቹን ተከትሎ ኢትዮጵያ ያገኘቻቸው የወርቅ ሜዳሊያዎች ብዛት አምስት ደርሰዋል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው አምስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና አምስት የነሐስ በድምሩ 11 ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። ሻምፒዮናው ነገ ይጠናቀቃል።