ቀጥታ፡
ስፖርት
ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከ52 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ አለፈች
Apr 1, 2026 86
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የክፍለ አህጉራት የመጨረሻ ማጣሪያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ጃማይካን 1 ለ 0 አሸንፋለች።   ከእኩለ ሌሊት በኋላ በሜክሲኮ አክሮን ስታዲየም የተካሄደው ጨዋታ መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ግብ አቻ በመጠናቀቁ ወደ ጭማሪ ሰዓት አምርቷል። በጭማሪ ሰዓት የተከላካይ መስመር ተጫዋቹ አክሴል ቱዋንዜቤ በ100ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። የጨዋታው ኮከብም ሆኗ ተመርጧል። በጨዋታው የማዕከላዊ አፍሪካዊቷ ሀገር የተሻለ ብልጫ በመውሰድ ተጫውታለች።   ውጤቱን ተከትሎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከ52 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫ በማለፍ ታሪክ ሰርታለች። የማዕከላዊ አፍሪካዊቷ ሀገር ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ1974 በጀርመን (በወቅቱ አጠራሯ ምዕራብ ጀርመን) አስተናጋጅነት በተካሄደው 10ኛው የዓለም ዋንጫ ነው። አሁን ለሁለተኛ ጊዜ በውድድሩ ላይ ትከፈላለች። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የምትሳተፍ 10ኛ የአፍሪካ ሀገርም ሆናለች። ሞሮኮ፣ ሴኔጋል፣ ግብጽ፣ ኮትዲቯር፣ አልጄሪያ፣ ቱኒዚያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ጋና እና ኬፕ ቨርዴ ለዓለም ዋንጫ ያለፉ የአፍሪካ ሀገራት ናቸው። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በዓለም ዋንጫው በምድብ 11 ከፖርቹጋል፣ ኡዝቤኪስታን እና ኮሎምቢያ ጋር ጨዋታዎቿን ታደርጋለች። አፍሪካ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ 10 ሀገራት በዓለም ዋንጫው ታሳትፋለች። ጃማይካ ከ28 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫው የመመለስ ውጥኗ አልተሳካም።
ጣልያን ከዓለም ዋንጫ ውጭ ሆነች
Apr 1, 2026 63
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ዞን የፍጻሜ ማጣሪያ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። ትናንት ማምሻውን በቢሊኖ ፖልጄ ስታዲየም በተካሄደውጨዋታ ቦስኒያ እና ሄርዞጎቪና ጣልያንን 4 ለ 1 በመለያ ምት አሸንፋለች። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሃሪስ ታባኮቪች ለቦሲኒያ፣ ሞይስ ኪን ለጣልያን ግቦቹን አስቆጥረዋል። የጣልያኑ አሌሳንድሮ ባስቶኒ በ41ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በጭማሪ 30 ደቂቃ ተጨማሪ ጎል ባለመቆጠሩ አሸናፊውን በመለያ ምት መለየት ግድ ሆኗል። በዚህ ቦሲኒያ 4 ለ 1 በማሸነፍ ከ12 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫው ማለፏን አረጋግጣለች። ሶስት ሚሊዮን ህዝብ ያላት ቦሲኒያ ለሁለተኛ ጊዜ በዓለም ዋንጫው ትሳተፋለች። ጣልያን ከ20ኛው የዓለም ዋንጫ በኋላ ዓለም ትልቁ የእግር ኳስ መድረክ የመመለስ ህልሟ አልተሳካም። አዙሪዎቹ ለሶስት ተከታታይ የዓለም ዋንጫ ማለፍ አልቻሉም።   በሌላኛው ጨዋታ ስዊድን ፖላንድን 3 ለ 2 አሸንፋለች። በስትሮውበሪ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶኒ ኢላንጋ፣ ጉስታፍ ላገርቢልክ እና ቪክቶር ዮኮሬሽ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የአርሰናሉ አጥቂ ዮኮሬሽ በ88ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ ስዊድንን ለዓለም ዋንጫ አሳልፏታል። ኒኮላ ዛሌውስኪ እና ካሮል ስዊዴርስኪ ለፖላንድ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።   በፋዲል ቮክሪ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቱርክዬ ኮሶቮን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ኬረም አክቱርኮግሉ ግቧን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ቼክ ሪፐብሊክ ዴንማርክን በመለያ ምት 3 ለ 1 አሸንፋለች። ሁለቱ ቡድኖች በ12ዐ ደቂቃ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። በኢፒኢቲ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፓቬል ሱልች እና ላዲስላቭ ክሬጄቺ ለቼክ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዮአኪም አንደርሰን እና ካስፐር ዋርትስ ሆግ ለዴንማርክ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጨዋታው በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ በመጠናቀቁ ምክንያት ወደ ጭማሪ ሰዓት አምርቷል። ላዲስላቭ ክሬጄቺ ለቼክ፣ ዋርትስ ሆግ በጭማሪ ሰዓት ግብ አስቆጥረዋል። ቡድኖቹ ወደ መለያ ምት አምርተው ቼክ ሪፐብሊክ 3 ለ 1 በማሸነፍ ለዓለም ዋንጫ አልፋለች። ውጤቱን ተከትሎ ስዊድን፣ቱርክዬ፣ቼክ ሪፐብሊክ እና ቦሲኒያና ሄርዞጎቪና ለ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ አልፈዋል። አራቱ ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራት ተቀላቅለዋል። አውሮፓ በዓለም ዋንጫው 16 ሀገራትን ታሳትፋለች።
ኢራቅ ከ40 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫ ተመልሳለች
Apr 1, 2026 65
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የክፍለ አህጉራት የፍጻሜ ማጣሪያ ኢራቅ ቦሊቪያን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ዛሬ ማለዳ ላይ በሜክሲኮ በቢቢቪኤ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አሊ አል ሃማዲ እና አይማን ሁሴን የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሞሰስ ፓኒያጉዋ ለቦሊቪያ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ቦሊቪያ የተሻለ ብልጫ የነበራት ቢሆንም ኢራቅ ከፈጠረቻቸው ሶስት ኢላማቸውን የጠበቁ ሙከራዎች መካከል ሁለቱን ወደ ግብ በመቀየር ውጤታማ ሆናለች። ግብ ያስቆጠረው የኢራቁ አይማን ሁሴን የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጧል። ኢራቅ ከ40 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ አልፋለች። የሜሶፖታሚያ አንበሶች ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፉት እ.አ.አ በ1986 ሜክሲኮ ባዘጋጀችው 11ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ነበር። ኢራቅ በውድድሩ ላይ ለሁለተኛ ጊዜ ትሳተፋለች። ቦሊቪያ ከ32 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ የማለፍ ህልሟ አልተሳካም። ለመጨረሻ በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ1994 በአሜሪካ በተዘጋጀው 15ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ላይ ነው። ትናንት ከእኩለ ሌሊት በኋላ በሜክሲኮ አክሮን ስታዲየም በተካሄደው የክፍለ አህጉራት የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ጃማይካን 1 ለ 0 በማሸነፍ ከ52 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ትልቁ የእግር ኳስ መድረክ ተመልሳለች። በአውሮፓ ትናንት ማምሻውን የተካሄዱ የጥሎ ማለፍ ማጣሪያ ጨዋታዎችን ተከትሎ ስዊድን፣ ቱርኪዬ፣ ቼክ ሪፐብሊክ እና ቦሲኒያና ሄርዞጎቪና ለዓለም ዋንጫ አልፈዋል። ጣልያን በመለያ ምት ተሸንፋ ከ12 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫ የመመለስ ህልሟ ተጨናግፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ ለዓለም ዋንጫ ያለፉ ሀገራት ሙሉ ለሙሉ ተለይተዋል።   23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ከሰኔ 4 እስከ ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም በአሜሪካ፣ ሜክሲኮ እና ካናዳ ጣምራ አዘጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ 48 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ሮቤርቶ ዴ ዘርቢ የቶተንሃም ሆትስፐርስ አሰልጣኝ ሆነው ተሾሙ 
Mar 31, 2026 155
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ ቶተንሃም ሆትስፐር ጣልያናዊውን አሰልጣኝ ሮቤርቶ ዴ ዘርቢን በአምስት ዓመት ኮንትራት አዲሱ ዋና አሰልጣኝ አድርጎ መሾሙን ዛሬ ይፋ አድርጓል። ክለቡ ይህንን ውሳኔ ያሳለፈው የቀድሞው ጊዜያዊ አሰልጣኝ ኢጎር ቱዶር በቆይታቸው ደካማ ውጤት በማስመዝገባቸውና ክለቡን ለወራጅ ቀጠና ስጋት ይበልጥ ማጋለጣቸውን ተከትሎ መሆኑን ስካይ ስፖርትስ ዘግቧል። የ46 ዓመቱ አሰልጣኝ ዴ ዘርቢ ከክለቡ አመራሮች ጋር ባደረጉት ስምምነት መሰረት እስከ 2031 ድረስ በለንደኑ ክለብ ለመቆየት ፊርማቸውን አኑረዋል። ዴ ዘርቢ ክለቡን በአሰልጣኝነት የተረከቡት ከፈርንሳዩ ማርሴይ ጋር በጋራ ስምምነት መለያየታቸውን ተከትሎ ነው። በውላቸው ላይ ክለቡ ወደ ታችኛው ሊግ ቢወርድ እንኳ ኮንትራቱን የሚያቋርጥ አንቀጽ (relegation clause) አለማካተቱ፣ በአሰልጣኙ ላይ ያለውን የረጅም ጊዜ እምነት እንደሚያሳይ ተገልጿል። ዴ ዘርቢ የክለቡ አሰልጣኝ ከሆኑ በኋላ በሰጡት መግለጫ ቶተንሃምን የመሰለ ታላቅ ክለብ በመቀላቀላቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። የክለቡ አመራሮች ያላቸው የወደፊት ራዕይ እና የሚከተሉት የማጥቃት እግር ኳስ ፍልስፍና ወደ ክለቡ እንዲመጡ እንዳነሳሳቸው ተናግረዋል። አሰልጣኙ ደጋፊዎችን የሚያስደስት ጨዋታ ለማሳየት ቃል ገብተዋል። የአሰልጣኙ አፋጣኝ እና ቀዳሚ ተግባር ቶተንሃም በዘንድሮው የውድድር ዘመን በፕሪምየር ሊጉ እንዲቆይ ማድረግ ነው። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ30 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። 18ኛ ደረጃ ላይ ከሚገኘው ዌስትሃም ዩናይትድ የሚበልጠው በአንድ ነጥብ ነው። ክለቡ ባለፉት 13 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ቀሪዎቹ ሰባት ጨዋታዎች ለአሰልጣኙ ትልቅ ፈተና እንደሚሆኑ ይጠበቃል። ሮቤርቶ ዴ ዘርቢ የመጀመሪያ የሊግ ጨዋታቸውን የሚያደርጉት ሚያዝያ 4 ቀን 2018 ዓ.ም ከሰንደርላንድ ጋር በ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ነው። እስከ ውድድር ዘመኑ ፍጻሜ ድረስ ክለቡን በደረጃ ሰንጠረዡ ከፍ ለማድረግ በሙሉ ትኩረት እና ትጋት እንደሚሰሩ አሰልጣኝ ዴ ዘርቢ አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ ወደ ምድብ ማጣሪያው አለፈች
Mar 31, 2026 155
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ኢትዮጵያ ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔን 1 ለ 0 አሸንፋለች። በድሬዳዋ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቸርነት ጉግሳ በሰባተኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ዋልያዎቹ በጨዋታው ላይ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድሎችን በመፍጠር የተሻሉ ነበሩ። ከእረፍት መልስ ቸርነት ጉግሳ ያልተጠቀመባት ግልጽ የግብ እድል በጨዋታው ተጠቃሽ ከሚባሉ ክስተቶች መካከል አንዱ ነው። በርካታ ደጋፊዎች በድሬዳዋ ስታዲየም በመገኘት ጨዋታውን ተከታትለውታል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ በድምር ውጤት በማሸነፍ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ወደ ምድብ ድልድል ማለፏን አረጋግጣለች። ብሔራዊ ቡድኑ በመጀመሪያው ጨዋታ 3 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣሪያ ከመስከረም እስከ ህዳር ወር 2019 ዓ.ም ይካሄዳል። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ በ2027 በታንዛንያ፣ ኬንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታዋን ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ታደርጋለች 
Mar 31, 2026 125
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታዋን ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ዛሬ ያከናውናል። የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታ በድሬዳዋ ስታዲየም ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ይካሄዳል። ሀገራቱ መጋቢት 18 ቀን 2018 ዓ.ም በሞሮኮ ኤል አብዲ ስታዲየም ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ 3 ለ 0 ማሸነፏ ይታወቃል። አቤል ያለው ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ከነዓን ማርክነህ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ በአሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ የሚመሩት ዋልያዎቹ ወደ ምድብ ድልድል የመግባት እድላቸውን አስፍተዋል። ብሔራዊ ቡድኑ ለመልሱ ጨዋታ ዝግጅት መጋቢት 20 ቀን 2018 ዓ.ም ድሬዳዋ የደረሰ ሲሆን የመጨረሻ ልምምዱን ጨዋታው በሚካሄድበት ድሬዳዋ ስታዲየም ትናንት ማምሻውን አድርጓል። አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ከጨዋታው በፊት ትናንት በሰጡት መግለጫ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ላይ ባገኘው ድል ሳይዘነጋ የመልሱን ጨዋታ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንደሚገባ ገልጸዋል። አሰልጣኙ ቢኒያም አይተን በጉዳት ምክንያት ከነገው ጨዋታ ውጪ መሆኑን ጠቁመዋል። ከቢኒያም ውጪ ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ በጤንነት ላይ መሆናቸውን አንስተዋል። በአባቱ ድንገተኛ ህልፈት ምክንያት በመጀመሪያው ጨዋታ ያልነበረው የቡድኑ አምበል ጋቶች ፓኖም ለመልሱ ጨዋታ ከብሔራዊ ቡድኑ ጋር በመቀላቀል ልምምድ ማድረጉን አመልክተዋል። በ47 ዓመቱ ፓርቹጋላዊ ሪካርዶ ሞናሳንቶ የሚመራው የሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ብሔራዊ ቡድን ጨዋታውን ለማድረግ ከትናንት በስቲያ ድሬዳዋ መግባቱ ይታወቃል። የመጨረሻ ልምምዱንም ትናንት በድሬዳዋ ስታዲየም ሰርቷል። ካፍ የነገው የኢትዮጵያ እና ሳኦቶሜ ጨዋታ በዝግ እንዲካሄድ ውሳኔ አሳልፎ ነበር። የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በስታዲየሙ ዙሪያ የተሰጡ የግምገማ አስተያየቶችን መሰረት በማድረግ በፍጥነት ለማስተካከል እርምጃ ወስዷል። የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ከከተማ አስተዳደሩ እርምጃ ጎን ለጎን ጨዋታው ለተመልካች ክፍት እንዲሆን ባደረገው ከፍተኛ ጥረት እንዲሁም የካፍ ሴኪዩሪቲ ኦፊሰር በአካል ተገኝተው ከገመገሙ በኋላ በላኩት ሪፖርት መሰረት ካፍ 10 ሺህ ተመልካች በስታዲየም ተገኝቶ እንዲከታተል ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቋል። ኢትዮጵያ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈች ወደ ምድብ ድልድል ምዕራፍ ማለፏን ታረጋግጣለች።
ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከ52 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ ታልፍ ይሆን?   
Mar 31, 2026 124
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018(ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የሚሳተፉ ቀሪ ሀገራት የሚለዩባቸው የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች የተመልካቾችን ትኩረት ስበዋል። በዓለም ዋንጫው የክፍለ አህጉራት የፍጻሜ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። አፍሪካዊቷ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከጃማይካ ጋር ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት በሜክሲኮ አክሮን ስታዲየም ይጫወታሉ። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ (48ኛ) በመያዟ ቀጥታ ለዛሬው የፍጻሜ ጨዋታ አልፋለች። ጃማይካ በግማሽ ፍጻሜው ኒው ካሌዶኒያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። የማዕከላዊ አፍሪካዊቷ ሀገር ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ1974 በጀርመን (በወቅቱ አጠራሯ ምዕራብ ጀርመን) አስተናጋጅነት በተካሄደው 10ኛው የዓለም ዋንጫ ነው። ውድድሩ የሀገሪቷ ብቸኛ የዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ነው። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ካሸነፈች ከ52 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫ በማለፍ ታሪክ የመስራት እድል ታገኛለች። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የምትሳተፍ 10ኛ የአፍሪካ ሀገር ትሆናለች። ሞሮኮ፣ ሴኔጋል፣ ግብጽ፣ ኮትዲቯር፣ አልጄሪያ፣ ቱኒዚያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ጋና እና ኬፕ ቨርዴ ለዓለም ዋንጫ ያለፉ የአፍሪካ ሀገራት ናቸው። በሌላኛው መርሐ ግብር ቦሊቪያ ከኢራቅ ነገ ማለዳ 12 ሰዓት ላይ በቢቢቪኤ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢራቅ ኮንጎ በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ (55ኛ) በመያዟ ለጥሎ ማለፍ የፍጻሜ ጨዋታው በቀጥታ አልፋለች። ቦሊቪያ በግማሽ ፍጻሜ ማጣሪያው ሱሪናምን 2 ለ 1 በማሸነፍ ለወሳኙ ጨዋታ ደርሳለች። አሸናፊ ሀገራት ለዓለም ዋንጫው ያልፋሉ። በተያያዘም የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ዞን የጥሎ ማለፍ የፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ። ቦሲኒያ እና ሄርዞጎቪና ከጣልያን ጋር ምሽት 3 ሰዓት ከ45 ላይ በቢሊኖ ፖልጄ ስታዲየም ይጫወታሉ። የአራት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ጣልያን ከ12 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫው ለመመለስ የምታደርገው ጨዋታ ትኩረት ስቧል። አዙሪዎቹ ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፉት እ.አ.አ በ2014 ብራዚል ባዘጋጀችው 20ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ነው። ጣልያን ባለፉት ሁለት የዓለም ዋንጫዎች አለመሳተፏ በዓለም እግር ኳስ ውስጥ ትልቅ መነጋገሪያ የሆነ ጉዳይ ነው። በ48 ዓመቱ ጄናሮ ጋቱሱ የሚመራው የጣልያን ብሔራዊ ቡድን ወደ ዓለም ዋንጫው የሚያሳልፋትን ትኬት ለመቁረጥ ቦስኒያን መርታት ይጠበቅበታል። በሌሎች መርሐ ግብሮች ስዊድን ከፖላንድ፣ ቼክ ሪፐብሊክ ከዴንማርክ እና ኮሶቮ ከቱርኪዬ በተመሳሳይ ምሽት 3 ሰዓት ከ45 ላይ ይጫወታሉ። በጥሎ ማለፉ የሚያሸንፉ አራት ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ። አውሮፓ በ23ኛው የዓለም ዋንጫ 16 ሀገራትን ተሳትፋለች።
ካፍ የኢትዮጵያ እና የሳኦቶሜና ፕሪንሲፔ ጨዋታን 10 ሺህ ተመልካች ስታዲየም ተገኝቶ እንዲከታተለው ወሰነ
Mar 30, 2026 195
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከሳኦቶሜና ፕሪንሲፔ አቻው ጋር የሚያደርገውን የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ 10 ሺህ ተመልካች በድሬዳዋ ስታዲየም ተገኘቶ እንዲከታተለው መወሰኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታወቀ። ካፍ የነገው የኢትዮጵያ እና ሳኦቶሜ ጨዋታ በዝግ እንዲካሄድ ውሳኔ አሳልፎ ነበር። የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በስታዲየሙ ዙሪያ የተሰጡ የግምገማ አስተያየቶችን መሰረት በማድረግ በፍጥነት ለማስተካከል እርምጃ መውሰዱን ፌዴሬሽኑ አመልክቷል። የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ከከተማ አስተዳደሩ እርምጃ ጎን ለጎን ጨዋታው ለተመልካች ክፍት እንዲሆን ባደረገው ከፍተኛ ጥረት እንዲሁም የካፍ ሴኪዩሪቲ ኦፊሰር በአካል ተገኝተው ከገመገሙ በኋላ በላኩት ሪፖርት መሰረት ካፍ 10 ሺህ ተመልካች በስታዲየም ተገኝቶ እንዲከታተል ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቋል። የሁለቱ ቡድኖች የመልስ ጨዋታ ነገ ከቀኑ 10 ሰዓት በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል።
ባስመዘገብነው የመጀመሪያ ድል ሳንዘናጋ የመልሱን ጨዋታ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንገባለን - አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ  
Mar 30, 2026 182
ድሬዳዋ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ላይ ባገኘው ድል ሳይዘነጋ የመልሱን ጨዋታ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንደሚገባ የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ተናገሩ። አሰልጣኝ ዮሐንስ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ የሚደረገውን የመልስ ጨዋታ አስመልክቶ ዛሬ በድሬዳዋ ስታዲየም ለመገናኛ ብዙሃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። አሰልጣኙ በመግለጫቸው ዋልያዎቹ የቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታን ለማሸነፍ የሚያስችላቸውን ዝግጅት አድርገዋል ሲሉ ገልጸዋል። ዋልያዎቹ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ሞሮኮ ላይ ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ 3 ለ 0 ማሸነፋቸውን አስታውሰው፤ ይህ ውጤት በምንም መንገድ መዘናጋት ሳይፈጥር ነገ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንገባለን ብለዋል። የብሔራዊ ቡድኑ ተጫዋቾች በጥሩ የማሸነፍ መንፈስ ታጅበው እንደሚጫወቱ ተናግረዋል። ተጫዋቾቹ በቂ ልምምድ ማካሄዳቸውንና በስነ-ልቦናም ጭምር ማሸነፍ የሚያስችላቸውን ዝግጅት ማድረጋቸውንም ነው የገለጹት። በአባቱ ድንገተኛ ህልፈት ምክንያት በመጀመሪያው ጨዋታ ያልነበረው የቡድኑ አምበል ጋቶች ፓኖም ለመልሱ ጨዋታ ከብሔራዊ ቡድኑ ጋር በመቀላቀል ልምምድ ማድረጉን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ነገ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር የሚካሄደውን የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ካሸነፈ ወደ ምድብ ድልድሉ ይቀላቀላል። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምስራቅ አፍሪካ አገራት በሆኑት ኬንያ፣ ታንዛኒያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት እ.አ.አ ጁን 2027 ይካሄዳል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የ55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና አጠቃላይ አሸናፊ ሆነ
Mar 29, 2026 303
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ ከመጋቢት 15 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በአደይ አበባ ዓለም አቀፍ ስታዲየም ሲካሄድ የቆየው 55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ተጠናቋል። በሻምፒዮናው ላይ 36 ክለቦች፣ ተቋማት፣ 9 ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተሳተፉ ሲሆን፤ 621 ወንድ፣ 436 ሴት በድምሩ 1057 ተወዳዳሪዎች ተሳትፈዋል።   ሻምፒዮናው ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት፣ ለአትሌቶች የውድድር እድል ለመፍጠር ፣ አትሌቶችን በሽልማት የማበረታታት ዓላማ ያለው ነው። በውድድሩ ማብቂያ ቀን 10 የፍጻሜ ውድድሮች ተካሄደዋል።   ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሻምፒዮናው አጠቃላይ አሸናፊ በመሆን አጠናቋል። መቻል ሁለተኛ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሶስተኛ ደረጃን ይዘው መጨረሳቸውን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በሻምፒዮናው መዝጊያ ላይ የተገኙት የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ኮማንደር ስለሺ ስህን እና ሌሎች የፌዴሬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች ለክለቦች እና አትሌቶች የተዘጋጁ የገንዘብ፣ የዋንጫና ሜዳሊያ ሽልማቶችን አበርክተዋል። ፌዴሬሽኑ ለውድድሩ ለማካሄድ 10 ሚሊዮን ብር ወጪ ማድረጉን አስታውቋል።   ዘመናዊ የሰዓት መመዝገቢያ ማሽን (Time Tronics) በሻምፒዮናው ላይ ተግባራዊ ሆኗል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ፌዴሬሽኑ በየዓመቱ ከሚያካሂዳቸው ውድድሮች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው።
ዋልያዎቹ ከሞሮኮ መልስ የመጀመሪያ ልምምዳቸውን አድርገዋል
Mar 29, 2026 217
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ለሚያደርገው የመልስ ጨዋታ የመጀመሪያ ልምምዱን ማምሻውን በድሬዳዋ ስታዲየም ሰርቷል።   በአባቱ ድንገተኛ ህልፈተ ሕይወት ምክንያት በመጀመሪያው ጨዋታ ያልነበረው የብሔራዊ ቡድኑ አምበል ጋቶቾ ፓኖም ስብስቡን ተቀላቅሎ ልምምድ አድርጓል። የዋልያዎቹ ተጋጣሚ የሆኑት ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ዛሬ ከቀትር በኋላ ድሬዳዋ መግባታቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።   የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች የመልስ ጨዋታ ማክሰኞ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ ከትናንት በስቲያ ሞሮኮ ላይ በተካሄደው የመጀመሪያ ጨዋታ 3 ለ 0 አሸንፋለች።   በአሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ የሚመራው ብሔራዊ ቡድን በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ ወደ ምድብ ድልድል መግባቱን ያረጋግጣል።   36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ በ2027 በታንዛንያ፣ ኬንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት ይካሄዳል።
በጅማ ዞን የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን የማስፋፋት ተግባር እየተከናወነ ነው
Mar 29, 2026 228
ጅማ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፡- በሥነ-ምግባርና በአካል የበቁ ወጣቶችን ለማፍራት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን የማስፋፋት ተግባር በትኩረት እያከናወነ መሆኑን የጅማ ዞን አስታውቋል።   32ኛው መላው የጅማ ዞን ስፖርት ሻምፒዮና በጅማ ከተማ መካሄድ የጀመረ ሲሆን፤ ሻምፒዮናው በእግር ኳስ፣ በማርሻል አርት እና በሌሎች 13 የስፖርት ዓይነቶች ለ15 ቀናት መካሄዱን ይቀጥላል።   የዞኑ ምክትል አሥተዳዳሪ ዩሱፍ ሻሮ በዚሁ ወቅት፤ ዞኑ የስፖርት ማዘውተሪያዎችን በመገንባትና ውድድሮችን በማዘጋጀት በሀገርና በክልል ደረጃ ተወዳዳሪ ብሎም ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት እየሠራ ነው ብለዋል። የጅማ ዞን ወጣቶችና ስፖርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ነጉማ መኮንን እንዳሉት፤ በስፖርት ሻምፒዮናው ከሁሉም የዞንና ወረዳዎች የተውጣጡ 1 ሺህ 800 ወጣቶች እየተሳተፉ ነው።   በውድድሩ ዞኑን ወክለው በክልል ደረጃ የሚሰለፉ ስፖርተኞች እንደሚመረጡም ጠቁመዋል።   ስፖርታዊ ሁነቶችን የምናካሂደው ሰላማችንን አስጠብቀን ስንቀጥል በመሆኑ፤ ለሰላም እና ለሀገር አንድነት ቅድሚያ ሰጥቶ መሥራት ይገባል ያሉት ደግሞ የኦሮሚያ ክልል የሥራና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ባይሳ ኩማ ናቸው።
ፌስቲቫሉ ኅብረ-ብሔራዊ አንድነት የሚጠናከርበትና አብሮነት የሚደምቅበት ነው
Mar 29, 2026 115
ሐረር፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፡- የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ኅብረ-ብሔራዊ አንድነት የሚጠናከርበት፣ የብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ዕሴትና አብሮነት የሚደምቅበት ነው ሲሉ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለጹ። 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድርና 19ኛው የባህል ስፖርት ፌስቲቫል "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሐሳብ በሐረር ከተማ ተጀምሯል፡፡   ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን በወቅቱ እንዳሉት፤ የኅብረ-ብሔራዊ አንድነትና አብሮነት መጠበቅና መረጋገጥ የባህል ስፖርቶችን አጉልቶ ለማሳየት ጠቃሚ ነው። የበለጠ እንዲጎለብትም መንግሥት ልዩ ትኩረት እንደሰጠው ተናግረዋል፡፡ የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴዔታ መክዩ መሀመድ በበኩላቸው፤ መንግሥት የባህል ስፖርትን ቀጣናዊ ትስስርን ለማምጣት፣ ወንድማማችነትንና እህትማማችነትን ለማጠናከር እየሠራበት ነው ብለዋል።   ኢትዮጵያ የ2026 የአፍሪካ የባህል ስፖርት ፌስቲቫልን የማስተናገድ ዕድል ማግኘቷንም አውስተዋል። ይህን ዕድል በመጠቀምም የባህል ስፖርቶቻችንን ለአፍሪካ እህት ወንድሞቻችን ለማስተዋወቅ ሥራዎች እየተሠሩ ነው ብለዋል። በሀገሪቱ ከ293 በላይ የተመዘገቡ ባህላዊ ስፖርቶችና ጨዋታዎች እንዳሉ በጥናት መለየቱን አረጋግጠዋል። ይሁን እንጅ የጨዋታ ሕግና ሥርዓት ተዘርግቶላቸው ለውድድር የበቁት ከ11 የስፖርት ዓይነቶች እንደማይበልጡ ጠቁመው፤ በቀጣይ ይህን ለማስፋት እንደሚሠራ አመላክተዋል። የባህል ስፖርት የሕዝብ ለሕዝብ ትስስርን በዘላቂነት በማጠናከር ረገድ ትልቁን ሚና እንደሚጫወት የገለፁት ደግሞ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርቶች ፌዴሬሽን ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሕይወት መሀመድ ናቸው፡፡ በሐረር ከተማ የተጀመረው የባህል ስፖርት ውድድርና ፌስቲቫል ለ8 ቀናት እንደሚቆይና ከመላ ሀገሪቱ የተውጣጡ ከ1 ሺህ 500 በላይ ስፖርተኞች ተሳትፎ እንደሚያደርጉበት ተናግረዋል።
ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል የመክፈቻ ስነ ስርዓት በሀረር ከተማ እየተካሄደ ነው 
Mar 29, 2026 113
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል የመክፈቻ ስነ ስርዓት በሀረር ከተማ ኢማም አህመድ ስታዲየም እየተካሄደ ይገኛል። ውድድር እና ፌስቲቫሉ የሚካሄደው "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ!" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው።   ስፖርታዊ ውድድሩ በሀረር ከተማ የተጀመረ ሲሆን በተለያዩ የጎዳና ላይ ትርዒቶችና የማርች ባንድ ሰልፍ ታጅቦ መካሄድ ጀምሯል። በውድድርና ፌስቲቫሉ መክፈቻ ላይ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ መኪዩ መሐመድ፣ የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ፣ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርቶች ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ወይዘሮ ህይወት መሐመድ እና የአፍሪካ ባህል ስፖርቶችና ጨዋታዎች ኮንፌዴሬሽን አመራሮች፣ የሁሉም ክልሎችና የሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች የወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊዎች፣ የክልሉ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ ከክልሉ የተለያዩ ወረዳዎች የተወጣጡ ነዋሪዎች ተገኝተዋል።   በ11 የስፖርት አይነት በሚካሄደው ውድድርና ፌስቲቫል ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ከ1500 በላይ ስፖርተኞች እንደሚሳተፉ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታውቋል። ፌስቲቫሉ ህብረተሰቡን በባህል ስፖርት ተሳታፊና ተጠቃሚ ከማድረግም ባሻገር የባህል ስፖርትን ማህበረሰብ አቀፍ የማድረግ አላማ ያለው ነው። ውድድሩና ፌስቲቫሉ እስከ መጋቢት 27 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ዛሬ ይጀመራል
Mar 29, 2026 182
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ከዛሬ ጀምሮ በሐረር ከተማ ይካሄዳል። የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን እና የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ስፖርታዊ ሁነቱን በጋራ አዘጋጅተዋል። ውድድሩና ፌስቲቫሉ "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ የሚደረግ ነው። በ11 የስፖርት አይነት በሚካሄደው ውድድርና ፌስቲቫል ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ከ1500 በላይ ስፖርተኞች እንደሚሳተፉ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታውቋል። በውድድርና ፌስቲቫሉ ላይ ከአፍሪካ ባህል ስፖርቶች እና ጨዋታዎች ኮንፌዴሬሽን የተጋበዙ የክብር እንግዶች ይታደማሉ። ሁነቱ የኢትዮጵያ ኅብረ ብሔራዊ አንድነት፣ ብዝሃነት እና አብሮነት የሚተዋወቅበት መሆኑ ተመላክቷል። ፌስቲቫሉ ህብረተሰቡን በባህል ስፖርት ተሳታፊና ተጠቃሚ ከማድረግም ባሻገር የባህል ስፖርትን ማህበረሰብ አቀፍ የማድረግ አላማ እንዳለው የሚኒስቴሩ መረጃ ያሳያል። መንግስት ለስፖርት ልማት በሰጠው ልዩ ትኩረት በአዲሱ የስፖርት ፖሊሲ አማካኝነት የባህል ስፖርቶችን ለማልማት እየሰራ እንደሚገኝም ተገልጿል።
ለቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ክለብ የ100 ሚሊየን ብር ድጋፍ ተደረገ
Mar 28, 2026 177
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ እና ቢጂአይ ኢትዮጵያ ለቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ክለብ የ100 ሚሊየን ብር ድጋፍ አደረጉ። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት የቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ክለብ ከገጠመው የመፍረስ አደጋ ለመታደግ የተለያዩ አካላትን በማስተባበር የ100 ሚሊየን ብር ድጋፍ መደረጉን አመልክተዋል።   ቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ የተጫዋቹ እና የማህበሩ ብቻ ሳይሆን አንዱ የከተማችን ጠንካራ ክለብ ነው ሲሉም ገልጸዋል። ኢትዮጵያንና ከተማዋን የወከለ ታሪካዊ የስፖርት ክለብ ከመፍረስ የመታደግ ኃላፊነት እንዳለብን እናምናለን ሲሉም ነው የተናገሩት ከንቲባዋ በመልዕክታቸው። ይህ አንጋፋ የስፖርት ክለብ ላለፋት 6 ወራት ደመወዝ መክፈል የማይችልበት ደረጃ ላይ ደርሶ እና የመበተን አደጋ ተጋርጦበት እንደነበር አውስተዋል።   በክለቡ ላይ የተጋረጠውን አደጋ ማየት ስለሌብን ከከተማው በጀትም ወስነን፣ ለባለሀብቶች ባቀረብነው ጥያቄ መሰረት ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ እና ቢጂአይ ኢትዮጵያ በሰጡን ፈጣን ምላሽ በጥቅሉ የ100 ሚሊየን ብር ድጋፍ ለተቋቋመው ጊዜያዊ ኮሚቴ አስረክበናል ነው ያሉት። ለከተማችን ወጣቶች፣ ለስፖርት ቢሮ እና ድጋፍ ላደረጉት ተቋማት በስፖርቱ ቤተሰብ ስም ምስጋናዬን ማቅረብ እወዳለሁ ሲሉም ገልጸዋል ከንቲባ አዳነች አቤቤ። ይህ ድጋፍ ከተማ አስተዳደሩ ክለቡን ከውድቀት ለመታደግና ለስፖርት ወዳድ ህዝብ የሰጠው ክብር አንዱ ማሳያ መሆኑንም ተናግረዋል።   ቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ክለብ ሁሉንም ባሳተፈ እና በግልፅነት አዲስ ቦርድ መርጦ ከገጠመው ጊዜያዊ ችግር ተላቆ ወደ ቀድሞ ጥንካሬውና ዝናው የሚመለስበት ጊዜ ቅርብ እንዲሆን እመኛለሁ ብለዋል ከንቲባዋ በመልዕክታቸው።
በክልሉ በስፖርት ዘርፍ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ -ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ
Mar 28, 2026 105
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በስፖርት ዘርፍ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በክልሉ ነገ የሚጀመረው 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል የዝግጅት ስራዎችን ተመልክተዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት በክልሉ በስፖርቱ ዘርፍ የሚከናወኑ ስራዎች በተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው፤ በዘርፉ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራትም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አንስተዋል።   በተለይ በክልሉና በአካባቢው በተለያዩ የስፖርት ዘርፍ ክህሎት ያላቸው ታዳጊ ስፖርተኞችን የማፍራት ስራ በትኩረት መስራት ይገባል ነው ያሉት። የሰርከስ ስፖርትን በማጎልበት በኩልም በሰፊው መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ከነገ ጀምሮ በሐረሪ ክልል ይካሄዳል። ለአንድ ሳምንት የሚቆየው የባህል ስፖርቶች ውድድር እና ፌስቲቫል "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ ይከናወናል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም