ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ሀዲያ ሆሳዕና ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Jan 16, 2026 32
አዲስ አበባ፤ ጥር 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሀዲያ ሆሳዕና ምድረገነት ሽሬን 3 ለ 1 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኤልያስ አሕመድ እና ሱራፌል ተመስገን በጨዋታ፣ ብሩክ በየነ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ተካልኝ ደጀኔ ለምድረገነት ሽሬ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሀዲያ ሆሳዕና በ20 ነጥብ ደረጃውን ከ15ኛ ወደ 9ኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ አምስተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ምድረገነት ሽሬ በ17 ነጥብ ከነበረበት 13ኛ ደረጃ ወደ 14ኛ ዝቅ ብሏል።
ነጌሌ አርሲ እና ወላይታ ድቻ አቻ ተለያዩ
Jan 16, 2026 46
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ነገሌ አርሲ እና ወላይታ ድቻ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ገ/መስቀል ዱባለ በ83ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ ነገሌ አርሲ መሪ ሆኗል። ሸገር ከተማ እና ፋሲል ከነማ ነጥብ ተጋሩ በፕሪሚየር ሊጉ ነጌሌ አርሲ ከወላይታ ድቻ ሸገር ከተማ ከፋሲል ከነማ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ ካርሎስ ዳምጠው በ94ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠረው ግብ ለወላይታ ድቻ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። ውጤቱን ተከትሎም አዲስ አዳጊው ነገሌ አርሲ በ26 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነትም ወደ አንድ ዝቅ የማድረግ ዕድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል። በሊጉ አምስተኛ ተከታታይ ድሉን የማስመዝገብ ሙከራውም አልተሳካም። ወላይታ ድቻ በ13 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኝ ሲሆን፤ ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም።
ሸገር ከተማ እና ፋሲል ከነማ ነጥብ ተጋሩ
Jan 16, 2026 49
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሸገር ከተማ እና ፋሲል ከነማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የፋሲል ከነማው የአማካይ ተጫዋች አቤኔዘር ዮሐንስ በ72ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ውጤቱን ተከትሎ ሸገር ከተማ በ15 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ፋሲል ከነማ በ26 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነትም ወደ አንድ ዝቅ የማድረግ እድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል።
120 ግቦች-የአፍሪካ ዋንጫ አዲስ ክብረ ወሰን
Jan 16, 2026 74
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡-በሞሮኮ አስተናጋጅነት ሲካሄድ የቆየው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የፊታችን እሁድ ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም ይጠናቀቃል። ሴኔጋል እና አዘጋጇ ሞሮኮ ዋንጫውን ለማንሳት ይፋለማሉ።24 ሀገራት በውድድሩ ላይ ተሳትፎ አድርገዋል። የአፍሪካ ዋንጫን የሚያሸንፈው ሀገር 10 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ያገኛል። ይህ በውድድሩ ታሪክ ትልቁ ሽልማት ነው። በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ የተመዘገበው ሌላኛው ክብረ ወሰን የተቆጠሩ ግቦች ናቸው። እስከ አሁን 50 ጨዋታዎች ተደርገው 120 ግቦች መቆጠራቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል።በአማካይ በየጨዋታው 2 ነጥብ 4 ግቦች ተቆጥረዋል። የፍጻሜ እና የደረጃውን ሳይጨምር እስከ አሁን ከመረብ ላይ ያረፉ 120 ግቦች እ.አ.አ በ2019 ግብጽ ባዘጋጀችው 32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የተቆጠሩትን 102 ጎሎች በመብለጥ አዲስ ክብረ ወሰን ሆኖ መመዝገቡን ካፍ ገልጿል። በምድብ 88፣ በጥሎ ማለፍ 21 እና በሩብ ፍጻሜ 10 ግቦችን ከመረብ ላይ ያረፉ ሲሆን በግማሽ ፍጻሜው አንድ ጎል ብቻ ተቆጥሯል። ናይጄሪያ በዘንድሮው ውድድር 14 ግቦችን በማስቆጠር ቀዳሚውን ስፍራ ይዛለች። ሴኔጋል በ12 ጎሎች ትከተላለች። ሞዛምቢክ ዘጠኝ ግቦችን በማስተናገድ ከፍተኛ ግብ የተቆጠረባት ሀገር ሆናለች።ሱዳን ስምንት እና ዩጋንዳ ሰባት ጎሎች ተቆጥሮባቸዋል። የተቆጠሩት ግቦች ብዛት የቡድኖችን የማጥቃት ፍላጎት፣ የቴክኒክ ብቃት እና የራስ መተማመን በግልጽ የሚያሳይ ነው። ይህም ብሄራዊ ቡድኖች ከጥንቃቄ ይልቅ ክፍት የጨዋታ ስልትን መምረጣቸው ለግቦቹ መበራከት አስተዋጽኦ አድርጓል። በውድድሩ ላይ የአፍሪካ ኃያላን ሀገራት በርካታ ግቦችን በማስቆጠር የቀዳሚነት ስፍራን ይዘዋል። የ26 ዓመቱ የሞሮኮ የክንፍ መስመር ተጫዋች ብራሂም ዲያዝ በአምስት ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። የናይጄሪያው ቪክቶር ኦሲሜን እና የግብጹ መሐመድ ሳላህ በተመሳሳይ አራት ግቦች ይከተላሉ። ሁለት ጨዋታው በቀረው የአፍሪካ ዋንጫ ክብረ ወሰኑ ከዚህም በላይ ሊሰፋ ይችላል። በጨዋታዎች ላይ የሚቆጠሩ ግቦች ለተመልካች ደስታ እና መዝናናትን ይሰጣሉ። ከቁጥሩ በላይ የዘንድሮ የአፍሪካ እግር ኳስ አሁን ያለበትን ደረጃ እና ቀጣይ መዳረሻውን የሚያመላክቱ ናቸው።
የተሻሻለው ሀገር አቀፍ የስፖርት ፖሊሲ የኢትዮጵያን ስፖርት ሁለንተናዊ እድገት የሚያረጋግጥ ነው
Jan 16, 2026 60
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡- የተሻሻለው ሀገር አቀፍ የስፖርት ፖሊሲ የኢትዮጵያን ስፖርት ልማትና ሁለንተናዊ እድገት የሚያረጋግጥ መሆኑን የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መኪዩ መሀመድ ገለጹ። የመደመር መንግሥት ለስፖርት ልማት ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ በመስራት ላይ ሲሆን በዚህ ረገድ በዘርፉ ተጨባጭ ለውጥ የሚያስገኙ እርምጃዎችን እየወሰደ ይገኛል። የዚሁ ማሳያ የሆነው የተሻሻለው ሀገር አቀፍ የስፖርት ፖሊሲ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ታህሳስ 28 ቀን 2018 ዓ.ም መጽደቁ ይታወሳል። ምክር ቤቱ ለ28 ዓመታት ያገለገለው ሀገር አቀፍ የስፖርት ፖሊሲ የተለያዩ ውስንነቶች የነበሩበት መሆኑን በመረዳት ይህን ሊቀርፍ በሚችል አግባብ እንዲሻሻል ወስኗል። የስፖርት ፖሊሲ ማሻሻያው ስፖርት ለሀገራዊ ብልፅግና እና ልማት ያለውን ድርሻ ማሳደግን ታሳቢ ባደረገ መልኩ መዘጋጀቱም ተገልጿል። የፖሊሲ ማሻሻያው በአደረጃጀት ለውጥ፣ስፖርቱን የዘርፉ እውቀትና ክህሎት ባለው ሰው መምራት፣የማኅበረሰቡ የስፖርት እንቅስቃሴ ተሳትፎ እና ዘርፉን ከመንግሥት በጀትና ድጎማ ማላቀቅ ላይ ያተኮረ ነው። ማሻሻያው የስፖርት ዘርፉ ያለውን ዘርፈ ብዙ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እንዲሁም አስተዳደራዊ ሂደትን ታሳቢ በማድረግ በአግባቡ ለመምራት እንዲሁም ዘመናዊ፣ አሳታፊና አካታች እንዲሆን ተደርጎ ጸድቋል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መኪዩ መሀመድ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት፤ የተሻሻለው ሀገር አቀፍ የስፖርት ፖሊሲ የስፖርቱን ማህበራዊ ልማትና ሁለንተናዊ እድገት የሚያረጋግጥ ነው። ፖሊሲው የተለያዩ ሀገራት ምርጥ ተሞክሮን ከሀገሪቱ ተጨባጭ ሁኔታ ጋር በማዋሃድ መዘጋጀቱን ጠቁመዋል። ፖሊሲው በዘርፉ የነበሩትን ክፍተቶች በዝርዝር መገምገሙን ገልጸው፤ በቀጣይ የሀገሪቱን ስፖርት ልማት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህ በፊት የነበረው የስፖርት ልማት ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ በመንግስት ይከናወን እንደነበር አስታውሰው፤ አዲሱ ፖሊሲ የግሉን ዘርፍ በስፋት ለማሳተፍ እድል የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል። አዲሱ ፖሊሲ የስፖርት ልማቱ በመንግስት፣ በህዝብና በግሉ ዘርፍ ቅንጅት እንዲከናወን ያስችላል ብለዋል። ፖሊሲው ስፖርትን ወደ ንግድ እንዲሁም ዓለም ዓቀፉ ነባራዊ ሁኔታ ወደ ደረሰበት ደረጃ ለማሳደግ በሚያስችል ሁኔታ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። ማሻሻያው የስፖርት መሰረተ ልማቶችን በማስፋፋት ዘርፉን ማሳደግ ላይ ማተኮሩን ጠቅሰው፤ ይህም በቀጣይ በሀገሪቱ የሚደረጉ ውድድሮች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን ጠብቀው የሚከናወኑበትን ዕድል እንደሚፈጥር አስታውቀዋል። በስፖርቱ ዘርፍ በጥናት የተደገፈ ሪፎርም መደረጉ በቀጣይ በተለያዩ ውድድሮች የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ ያስችላል ብለዋል፡፡ ፖሊሲው በሰው ኃብት ልማት፣ በፋይናንስ አቅርቦትና በማዘውተሪያ ቦታዎች ልማት ላይ ለሚታዩ ክፍተቶች ምላሽ እንዲሰጥ ተደርጎ መሻሻሉን ተናግረዋል። የተሻሻለው የስፖርት ፖሊሲ ማህበራዊ ልማትና ሁለንተናዊ እድገትን በሚያረጋግጥ እና ዓለም አቀፍ የስፖርት ልማት መለኪያ መስፈርቶችን በማሟላት መዘጋጀቱ ተገልጿል።
በዶሃ የማራቶን ውድድር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሁለቱም ጾታዎች አሸነፉ
Jan 16, 2026 71
አዲስ አበባ፤ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፦ዛሬ ማለዳ በኳታር ዶሃ በተካሄደው የማራቶን ውድድር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሁለቱም ጾታዎች አሸንፈዋል። በወንዶች ምድብ የተካሄደውን ውድድር የኦሎምፒክ ሻምፒዮኑ አትሌት ታምራት ቶላ የቦታውን ክብረ ወሰን በማሻሻል አሸንፏል። አትሌት ታምራት ውድድሩን ለማጠናቀቅ 2 ሰዓት ከ5 ደቂቃ 40 ሴኮንድ የፈጀበት ሲሆን ይህም የዶሃ ማራቶን የቦታው ክብረወሰን ሆኖ ተመዝግቧል። አትሌት ታምራት ቶላን በመከተልም አትሌት አሰፋ ቦኪ ሁለተኛ፤ ቦኪ ዲሪባ ሶስተኛ ፤ድንቃለም አየለ አራተኛ እንዲሁም ባለው ይሁኔ አምስተኛ ደረጃን በመያዝ በውድድሩ ላይ የኢትዮጵያን የበላይነት አሳይተዋል። በተመሳሳይ በሴቶች ምድብ በተካሄደው ውድድር አትሌት ትዕግስት ገዛኸኝ ውድድሯን በቀዳሚነት ያጠናቀቀች ሲሆን ፤ሌላኛዋ አትሌት ትዕግስት ግርማ ሁለተኛ እንዲሁም ሙሉሀብት ጸጋ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ የዶሃ ማራቶንን በበላይነት አጠናቀዋል።
በፕሪሚየር ሊጉ ነጌሌ አርሲ ከወላይታ ድቻ ሸገር ከተማ ከፋሲል ከነማ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Jan 16, 2026 76
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 15ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ነጌሌ አርሲ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ነጌሌ አርሲ በሊጉ ባደረጋቸው 14 ጨዋታዎች በሰባቱ ድል ሲቀናው በሶስቱ ተሸንፏል። አራት ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 16 ግቦችን ሲያስቆጥር ዘጠኝ ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ25 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ወላይታ ድቻ በሊጉ እስከ አሁን 14 ጨዋታዎች አከናውኖ ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በስድስቱ ተሸንፏል። በቀሪ ስድስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 14 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያገናኝ 18 ግቦች ተቆጥረውበታል። ወላይታ ድቻ በ12 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በጠንካራ ግስጋሴ ላይ የሚገኘው ነጌሌ አርሲ በሊጉ አምስተኛ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ባለፉት አራት ጨዋታዎች ያላሸነፈው ወላይታ ድቻ ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና ሊያወጣው የሚችልበት እድል አለ። በሌላኛው መርሃ ግብር ሸገር ከተማ ከፋሲል ከነማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በ14 የሊጉ ጨዋታዎች በሶስቱ ሲያሸንፍ ስድስት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ14ቱ ጨዋታዎች ላይ 12 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 16 ግቦች ተቆጥረውበታል። ሸገር ከተማ በ14 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ በውድድር ዓመቱ 14 ጨዋታዎች አድርጎ ስድስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሽንፈት ያጋጠመው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በሰባት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 10 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ አምስት ጎሎችን አስተናግዷል። ፋሲል ከነማ በ25 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ ያልቻለው ሸገር ከተማ ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና ስጋት በመጠኑም ቢሆን እንዲርቅ ያደርገዋል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ በ14ኛ ሳምንት ካስተናገደው የሊጉ የመጀመሪያ ሽንፈት በኋላ ወደ ድል መንገድ ለመመለስ ይጫወታል። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ሀዲያ ሆሳዕና ከምድረ ገነት ሽሬ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሀዲያ ሆሳዕና በ17 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ምድረ ገነት ሽሬ በተመሳሳይ 17 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ምሽት 12 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ22 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ17 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል።
ባህር ዳር ከተማ እና መቀሌ 70 እንደርታ አቻ ተለያዩ
Jan 15, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ እና መቀሌ 70 እንደርታ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታው በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተካሂዷል። ባህር ዳር ከተማ በ20 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። መቀሌ 70 እንደርታ በ13 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ዛሬ በተደረገ የ15ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ኢትዮጵያ መድን እና ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ነጥብ ተጋሩ
Jan 15, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን እና ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 15ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል ጨዋታው የተካሄደው በአዲስ አበባ ስታዲየም ነው። ውጤቱን ተከትሎም የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ17 ነጥብ ደረጃውን ከ15ኛ ወደ 11ኛ ከፍ ማድረግ ችሏል። በ12 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኘው ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ፤ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 15ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል
Jan 15, 2026 84
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ኢትዮጵያ መድን ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ መድን በሊጉ ባደረጋቸው 14 ጨዋታዎች በአራቱ አሸንፎ በስድስቱ ተሸንፌ በቀሪ አራት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 12 ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ መድን በ16 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በበኩሉ በ14 ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ ሰባት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። ስምንት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 17 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ወልዋሎ በ11 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኢትዮጵያ መድን ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ማሸነፍ ወደ አሸናፊነት መንገድ ይመልሰዋል። በሌላኛው መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከመቀሌ 70 እንደርታ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ 14 ጨዋታዎች አድርጎ አራት ጊዜ ድል ሲቀናው በሶስቱ ተሸንፏል። በሰባት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 11 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 10 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ19 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 14 ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን ብቻ ያሸነፈው መቀሌ 70 እንደርታ በስድስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ስድስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። በ14ቱ ጨዋታዎች 10 ግቦችን ሲያስቆጥር 19 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ 18ኛ ደረጃን በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ባህር ዳር ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ፣ መቀሌ 70 እንደርታ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 15ኛ ሳምንት እስከ ጥር 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ሲዳማ ቡና በ29 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ አጥቂ አዲስ ግደይ ሰባት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በመምራት ላይ ይገኛል።
በካራባኦ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ የመጀመሪያ ዙር ጨዋታ አርሰናል ቼልሲን አሸነፈ
Jan 15, 2026 137
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018 (ኢዜአ)፦ በካራባኦ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር አርሰናል ቼልሲን 3 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቤን ዋይት፣ ቪክቶር ዮኮሬሽ እና ማርቲን ዙቢሜንዲ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አሊሃንድሮ ጋርናቼ የቼልሲን ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፏል። አርሰናል በጨዋታው ላይ ተጨማሪ ግቦችን የማስቆጠር እድሎች አግኝቶ አልተጠቀመበትም። የቼልሲው አዲስ አሰልጣኝ ሊያም ሮሲናየር በመጀመሪያ ጨዋታቸው ሽንፈት አስተናግደዋል። የአርሰናሉ አጥቂ ቪክቶር ዮኮሬሽ የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። የሁለቱ ክለቦች የመልስ ጨዋታ ጥር 26 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ትናንት በካራባኦ ዋንጫ በተካሄደው ሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 0 አሸንፏል። የመልስ ጨዋታው ጥር 27 ቀን 2018 ዓ.ም ይደረጋል።
አዘጋጇ ሞሮኮ ለአፍሪካ ዋንጫ ፍጻሜ አለፈች
Jan 15, 2026 115
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ሞሮኮ ናይጄሪያን በመለያ ምት አሸንፋለች። ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም የተካሄደው ጨዋታ በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ግብ ባለመቆጠሩ 30 ደቂቃ ተጨምሯል። በ120 ደቂቃ ጨዋታው ያለ ግብ አቻ በመጠናቀቁ ወደ መለያ አምርቷል። በዚህም ሞሮኮ 4 ለ 2 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፋለች። በጨዋታው ላይ ሞሮኮ አንጻራዊ ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። አዘጋጇ ሞሮኮ በፍጻሜው ከሴኔጋል እሁድ ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም ጨዋታዋን ታደርጋለች። ሴኔጋል ዛሬ በተደረገ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ግብጽን 1 ለ 0 በማሸነፍ ለፍጻሜ ማለፏ ይታወቃል። የግማሽ ፍጻሜ ተሸናፊዎቹ ግብጽ እና ናይጄሪያ ቅዳሜ ጥር 9 ቀን 2018 ዓ.ም ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ይጫወታሉ።
ሴኔጋል ግብጽን በማሸነፍ ለአፍሪካ ዋንጫ ፍጻሜ አለፈች
Jan 14, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ሴኔጋል ግብጽን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በታንጀር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሳዲዮ ማኔ በ78ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ማኔ በውድድሩ ላይ ያስቆጠረውን ግብ ብዛት ወደ ሁለት ከፍ አድርጓል። በጨዋታው ሴኔጋል ከፍተኛ ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ግብጽ የጥልቀት መከላከል እና የመልሶ ማጥቃት የአጨዋወት ስልት ውጤታማ አልሆነም። ውጤቱን ተከትሎ የአንድ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋ ሴኔጋል ለፍጻሜ አልፋለች። በፍጻሜው ከናይጄሪያ እና ሞሮኮ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ናይጄሪያ እና ሞሮኮ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታቸውን ምሽት አምስት ላይ በፕሪንስ ሙላይ ስታዲየም ያደርጋሉ።
ቼልሲ እና አርሰናል በካራባኦ ዋንጫ የሚያደርጉት የግማሽ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 14, 2026 150
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር የግማሽ ፍፃሜ መርሃ ግብር ቼልሲ እና አርሰናል ዛሬ ይጫወታሉ። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ይካሄዳል። በሩብ ፍጻሜው ቼልሲ ካርዲፍ ሲቲን ፣ አርሰናል ክሪስታል ፓላስን በማሸነፍ የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብተዋል። ቼልሲ የካራባኦ ዋንጫን አምስት ጊዜ አንስቷል። የለንደን ጎረቤቱ አርሰናል ሁለት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሆኗል። የምዕራብ ለንደኑ ክለብ ቼልሲ ለመጨረሻ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ የነበረው እ.አ.አ በ2014/15 የውድድር ዓመት ነው። የሰሜን ለንደኑ አርሰናል እ.አ.አ 1992/93 ለመጨረሻ ጊዜ ዋንጫውን አንስቷል። ቡድኖቹ በካራባኦ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም እርስ በእርስ ባደረጓቸው ሶስት ጨዋታዎች ሁለቱ ክለቦች በተመሳሳይ አንድ ጊዜ ሲያሸንፉ በቀሪው ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። እ.አ.አ በ2018 በተመሳሳይ በግማሽ ፍጻሜ ተገናኝተው አርሰናል በድምር ውጤት 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። መድፈኞቹ በፍጻሜው በማንችስተር ሲቲ 3 ለ 0 ተሸንፈው ዋንጫውን አጥተዋል። አዲሱ የቼልሲ ሊያም ሮሲኒየር የመጀመሪያ ጨዋታቸውን ዛሬ ያደርጋሉ። የሁለቱ ክለቦች የመልስ ጨዋታ ጥር 26 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ትናንት በካራባኦ ዋንጫ በተደረገው የመጀመሪያ ዙር የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 0 አሸንፏል።
የአፍሪካ ዋንጫን የወርቅ ጫማ ማን ይወስዳል?
Jan 14, 2026 128
በሞሮኮ አስተናጋጅነት ታህሳስ 12 ቀን 2018 ዓ.ም የተጀመረው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ወደ መገባደዱ ላይ ደርሷል። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ሴኔጋል ከግብጽ ምሽት አንድ ሰዓት፣ ናይጄሪያ ከሞሮኮ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ ለፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ተጠባቂ ናቸው። በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ እስከ አሁን በተደረጉ 48 ጨዋታዎች 119 ግቦች ከመረብ ላይ አርፈዋል። በየጨዋታው በአማካይ 2 ነጥብ 48 ግቦችን ተቆጥረዋል። 119 ግቦች ኮትዲቯር ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ላይ ከተቆጠረው ተመሳሳይ የግብ መጠን ተስተካክሏል። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በውድድሩ ታሪክ በርካታ ግቦች የተቆጠሩበት ሆኖ እንደሚጠናቀቅ እርግጥ ነው። ጨዋታዎቹ በጎል የታጀቡ እና አዝናኝ እንቅስቃሴ ተደርጎባቸዋል። ከዋንጫው ፉክክር ባልተናነሰ የኮከብ ግብ አስቆጣሪነቱ ጉዳይ የእግር ኳስ አፍቃሪያን ትኩረት ስቧል። በውድድሩ ላይ ድንቅ ጊዜ እያሳለፈ የሚገኘው የሞሮኮው የክንፍ መስመር ተጫዋች ብራሂም ዲያዝ በአምስት ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ይገኛል። የናይጄሪያው ቪክቶር ኦሲሜን እና የግብጹ መሐመድ ሳላህ በተመሳሳይ አራት ጎሎችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ይከተላሉ። የሞሮኮው አዩብ ኤል ካቢ እና የናይጄሪያው አዴሞላ ሉክማን በተመሳሳይ ሶስት ግቦችን አስቆጥረዋል። ዛሬ ናይጄሪያ እና ሞሮኮ በሚያደርጉት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ የቪክቶር ኦሲሜን እና ብራሂም ዲያዝ ፍጥጫ ይጠበቃል። ሴኔጋል ከግብጽ በሚያከናውኑት ሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር የግብጹ መሐመድ ሳላህ የሚጠበቅ ይሆናል። የወርቅ ጫማውን ማን ይወስዳል? ለሚለው ጥያቄ ቀሪ አራት ጨዋታዎች ምላሽ ይሰጣሉ።
ኃያላኑን ያገናኘው የአፍሪካ ዋንጫ ተጠባቂ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር
Jan 14, 2026 131
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ሴኔጋል ከግብጽ ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ በታንጀር ስታዲየም ይጫወታሉ። በሩብ ፍጻሜው ሴኔጋል ማሊን፣ ግብጽ ኮትዲቯርን በማሸነፍ የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብተዋል። ሁለቱ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለስድስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው አምስት ጨዋታዎች ሴኔጋል በሶስቱ ድል ሲቀናት ግብጽ ሁለት ጊዜ አሸንፋለች። እ.አ.አ በ1986 ግብጽ ባዘጋጀችው 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው ሴኔጋል በቲርኖ ዩም ጎል 1 ለ 0 አሸንፋለች። በሀገራቱ የእርስ በእርስ ግንኙነት ውስጥ በዋናነት የሚነሳው ካሜሮን እ.አ.አ በ2021 ባዘጋጀችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዋንጫ ለማንሳት የተፋለሙበት ነው። ሴኔጋል በመለያ ምት 4 ለ 2 በማሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካን ዋንጫ አንስታለች። ግብጽ ለመጨረሻ ጊዜ ሴኔጋልን በአፍሪካ ዋንጫው ያሸነፈችው እ.አ.አ በ2006 ባዘጋጀችው 25ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በግማሽ ፍጻሜው ተገናኝተው ግብጽ በአህመድ ሀሰን እና አሚር ዛኪ ግቦች 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፋለች። ማማዱ ኒያንግ ለሴኔጋል ብቸኛውን ጎል ያስቆጠረ ተጫዋች ነው። ግብጽ በፍጻሜው ኮትዲቯርን በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ውድድሩን ሰባት ጊዜ በማሸነፍ ስኬታማዋ ሀገር ናት። ከቅርብ ዓመታት በአፍሪካ እግር ኳስ ውስጥ ተፎካካሪነታቸው እያደገ የመጣው ሁለቱ ሀገራት ለፍጻሜው ለማለፍ ጠንካራ ፍልሚያ ያደርጋሉ። በሊቨርፑል ማልያ አንድ ላይ የተጫወቱት ሳዲዮ ማኔ እና መሐመድ ሳላህ በጨዋታው ላይ ልዩነት ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ናይጄሪያ ከሞሮኮ ምሽት አምስት ላይ በፕሪንስ ሙላይ የሚያደርጉት ጨዋታም ተጠባቂ ነው። ናይጄሪያ በሩብ ፍጻሜው አልጄሪያን፣ ሞሮኮ ካሜሮንን በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል። ሀገራቱ በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለስድስተኛ ጊዜ ነው። የመጀመሪያ ጨዋታቸውን ያደረጉት ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1976 በተካሄደው 10ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው። በምድብ ሁለት ተገናኝተው ሞሮኮ 3 ለ 1 አሸንፋለች። አህመድ ፋራስ፣ አብደላ ታዚ እና ላርቢ ቼባክ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሳሙኤል ኦጄቦዴ ለናይጄሪያ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሞሮኮ ጊኒን በማሸነፍ ብቸኛውን ዋንጫ በወቅቱ አንስታለች። እ.አ.አ በ1980 በናይጄሪያ በተካሄደው 12ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በግማሽ ፍፃሜው ተገናኝተው አዘጋጇ ናይጄሪያ በግማሽ ፍጻሜው በፍሊክስ ኦዎላቢ ግብ 1 ለ 0 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፋለች። በፍጻሜው ናይጄሪያ አልጄሪያን 3 ለ 0 በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ብሄራዊ ቡድኖቹ ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ2004 በቱኒዚያ በተካሄደው 24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነበር። በምድብ አራት ባደረጉት ጨዋታ በዩሱፍ ሃጂ ጎል ሞሮኮ 1 ለ 0 አሸንፋለች። ሁለቱ ሀገራት አጠቃላይ አምስት ጊዜ ተገናኝተው ሞሮኮ ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ ናይጄሪያ ሁለት ጊዜ ድል ቀንቷታል። ከ22 ዓመታት በኋላ በአህጉራዊው መድረክ የሚገናኙት ሀገራቱ ለተመልካች አዝናኝ እና ተመጣጣኝ ፉክክር ያሳያሉ ተብሎ ይጠበቃል። አራት ግቦችን ያስጠቆጠረው ቪክቶር ኦሲሜን ከናይጄሪያ እና አምስት ግቦችን ከመረብ ጋር በማገናኘት ኮከብ ግብ አግቢነቱን የሚመራው ብራሂም ዲያዝ ከሞሮኮ በጨዋታው ልዩነት ይፈጥራሉ ተብሎ ይጠበቃል። የዛሬ ጨዋታ አሸናፊዎች ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም ዋንጫውን ለማንሳት ይፋለማሉ። ተሸናፊ ሀገራት ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ጥር 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይጫወታሉ። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በካራባኦ ዋንጫ ማንችስተር ሲቲ ድል ቀንቶታል
Jan 14, 2026 107
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሴይንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶዋን ሴሜንዮ በ53ኛው እና ራያን ቸርኪ በ98ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። በጨዋታው ላይ ማንችስተር ሲቲ ኢላማቸውን የጠበቁ የግብ ሙከራዎችን በሚገባ መጠቀሙ ባለድል አድርጎታል። በአንጻሩ ኒውካስትል ዩናይትድ ግልጽ የግብ እድሎችን አምክኗል። በጨዋታው ላይ አዲስ ፈራሚው ሴሜንዮ ጥሩ ብቃት ያሳየ ሲሆን የጨዋታው ኮከብ በመሆን ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ ወደ ፍጻሜ የማለፍ እድሉን አስፍቷል። በአንጻሩ የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ኒውካስትል ዩናይትድ ውጤቱን የመቀልበስ ጠንካራ የቤት ስራ ይጠብቀዋል። የሁለቱ ክለቦች የግማሽ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታ ጥር 27 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ሌላኛው የመጀመሪያ ዙር የካራባኦ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር በቼልሲ እና አርሰናል መካከል ነገ ይደረጋል።
ማይክል ካሪክ የማንችስተር ዩናይትድ ጊዜያዊ አሰልጣኝ ለመሆን ተስማማ
Jan 13, 2026 126
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ ማይክል ካሪክ ማንችስተር ዩናይትድን እስከ ውድድር ዓመቱ መጨረሻ በጊዜያዊነት ለማሰልጠን ከስምምነት ላይ ደርሷል። የ44 ዓመቱ እንግሊዛዊ የአሰልጣኝነቱን ቦታ ያገኘው የቀድሞው የዩናይትድ አሰልጣኝ ኦሌ ጉናር ሶልሻየር ጋር ተወዳድሮ ካሸነፈ በኋላ መሆኑን የእንግሊዙ ጋዜጣ ዘ ሰን ይዞት በወጣው መረጃ ገልጿል። ካሪክ ከዳረን ፍሌቸር ቦታውን በመረከብ ስራውን ነገ ጠዋት በይፋ ይጀምራል። ማንችስተር ዩናይትድ ፖርቹጋላዊውን አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን ባለፈው ሳምንት ማሰናበቱ ይታወቃል። የማንችስተር ዩናይትድ የቀድሞ ተጫዋች ካሪክ በ12 ዓመት የተጫዋችነት ቆይታው አምስት የፕሪሚየር ሊግ ጨምሮ 18 ዋንጫዎችን አንስቷል። ካሪክ እ.አ.አ በ2021 የዩናይትድ ጊዜያዊ አሰልጣኝ ሆኖ አገልግሎ ነበር። ከእ.አ.አ 2022 እስከ 2025 የሚድልስቦሮው ዋና አሰልጣኝ በመሆን ሰርቷል።
ከማላጋ እስከ አፍሪካ ዋንጫ፤ የሞሮኮው አዲስ እንቁ ብራሂም ዲያዝ
Jan 13, 2026 172
የግል ክህሎት፣ ፈጣን አስተሳሰቡ እና በጠባብ ክፍተቶች ውስጥ ሰብሮ የመግባት አቅሙ ሙገሳ እንዲጎርፍለት አድርጓል። አንድ ለአንድ ሲገናኝ ተከላካዮችን በፈጣን አካላዊ ቅልጥፍና እና በድንገት አቅጣጫ በመቀየር የሚያልፍበት መንገድ እንዲሁም የመፍጠር አቅሙ የተመልካቾችን ቀልብ የሚይዝ ነው። የአማካይ እና የአጥቂ መስመርን በማገናኘት እና በአስገራሚ ሁኔታ አጭር ኳሶችን በማቀበልም የተዋጣለት ተጫዋች ነው ማለት ይቻላል። በቦታ አያያዙ የእግር ኳስ ልኅቀቱ ከፍተኛ ነው የሚል አድናቆት ከእግር ኳስ ባለሙያዎች አግኝቷል። ኳስን ሲያንከባልልም ለዐይን ይስባል። ከክህሎቱ እና ከማራኪ እንቅስቃሴው ባለፈ ወደ ኋላ እየመለሰ ተከላካዮችን ያግዛል፣ ኳስ ይነጥቃል። ይህ ተጫዋች የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ክስተት የሆነው የሞሮኮው ብራሂም ዲያዝ ነው። የ26 ዓመቱ የሪያል ማድሪድ የክንፍ መስመር ተጫዋች ዲያዝ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ አምስት ጨዋታዎችን አድርጎ አምስት ግቦችን በማስቆጠር የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። አዘጋጇ ሞሮኮ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ መክፈቻ ኮሞሮስን 2 ለ 0 ስታሸንፍ የውድድሩን የመጀመሪያ ግብ አስቆጥሯል። ብራሂም አብዱልቃድር ዲያዝ የተወለደው እ.አ.አ ኦገስት 3 ቀን 1999 በስፔን ማላጋ ግዛት ነው። እናቱ ስፔናዊ አባቱ ሞሮኳዊ ናቸው። ዲያዝ ያደገው በማላጋ ነው። እግር ኳስንም በአንዳሉሺያዊቷ ከተማ ሲጫወት ቆይቷል። በ16 ዓመቱ ካደገበት ማላጋ በመውጣት እ.አ.አ በ2015 ወደ ማንችስተር ሲቲ ወጣት አካዳሚ በ200 ሺህ ፓውንድ ወጪ ተዘዋወረ። ዲያዝ እ.አ.አ ሴፕቴምበር 21 ቀን 2016 በካራባኦ ካፕ (በቀድሞ አጠራሩ ሊግ ካፕ) ማንችስተር ሲቲ ከስዋንሲ ሲቲ ባደረገው ጨዋታ በ80ኛው ደቂቃ በኬሌቺ ኢናቺዩ ተቀይሮ በመግባት ለውኃ ሰማያዊዎቹ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የመጀመሪያውን ጨዋታ ካደረገ ከሶስት ቀናት በኋላ ከማንችስተር ሲቲ ጋር ለሶስት ዓመታት የሚያቆየውን ፕሮፌሽናል ኮንትራት ተፈራርሟል። እ.አ.አ ኖቬምበር 21 ቀን 2017 ማንችስተር ሲቲ ከፌይኖርድ ሮተርዳም ጋር ባደረገው የሻምፒዮናስ ሊግ ጨዋታ ላይ የመጀመሪያ የአውሮፓ መድረክ ጨዋታውን ማድረግ ችሏል። በወቅቱ ብራሂም ስተርሊን መደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በጭማሪ ሰዓት ላይ ነበር ተቀይሮ የገባው። ዲያዝ በውኃ ሰማያዊዎቹ ማልያ ቋሚ አሰላለፍ ውስጥ ገብቶ የተጫወተው እ.አ.አ ዲሴምበር 19 ቀን 2017 ነው። ማንችስተር ሲቲ ከሌስተር ሲቲ በካራባኦ ካፕ ጨዋታ ላይ ለ88 ደቂቃዎች ተሰልፎ ተጫውቷል። እ.አ.አ ጃንዋሪ 20 ቀን 2018 ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 3 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። በወቅቱ ማንችስተር ሲቲ የሊጉን ዋንጫ ያነሳ ሲሆን፤ በውድድር ዓመቱ አራት ጨዋታዎች ላይ ብቻ ተሳትፎ ያደረገው ብራሂም ዲይዝ የሜዳሊያ ሽልማት አግኝቷል። እ.አ.አ ኦገስት 5 ቀን 2018 ማንችስተር ሲቲ ቼልሲን 2 ለ 0 ባሸነፈበት የኮሙዩኒቲ ሺልድ ጨዋታ ላይ በፊል ፎደን ተቀይሮ በመግባት ለ15 ደቂቃዎች ተጫውቷል። ዲያዝ እ.አ.አ 2018/19 ማብቂያ ላይ ማንችስተር ሲቲ ፉልሃምን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የመጀመሪያ ግቦቹን ለሲቲ አስቆጥሯል። በማንችስተር ሲቲ ያለው ውል እ.አ.አ 2019 ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ወቅት ስሙ ከዝውውር ጋር በስፋት ይነሳ ነበር። ዲያዝ እ.አ.አ ጥር 2019 በ17 ሚሊዮን ዩሮ ከማንችስተር ሲቲ ወደ ሪያል ማድሪድ ተዘዋወረ። ለስድስት ዓመታት የሚያቆየውን ውልም ፈርሟል። የክንፍ ተጫዋቹ የመጀመሪያ ጨዋታውን በነጮቹ ማልያ ያደረገው እ.አ.አ ጥር 9 ቀን 2019 ሪያል ማድሪድ ሌጋኔን በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ 3 ለ 0 ባሸነፈበት ወቅት ነው። ከአራት ቀናት በኋላ በስፔን ላሊጋ ሪያል ማድሪድ ሪያል ቤቲስን 2 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ ተቀይሮ በመግባት በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የመጀመሪያ ግቡን ለማስቆጠር ሶስት ወራትን ጠብቋል። እ.አ.አ ግንቦት 12 ቀን 2019 ሪያል ማድሪድ በላሊጋው በሪያል ሶሲዬዳድ 3 ለ 1 ሲሸነፍ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በወቅቱ ዲያዝ ስድስት ጨዋታዎች ላይ በላሊጋው የተጫወተ ሲሆን፤ በመጀመሪያ ዓመቱ የሊጉን ዋንጫ አንስቷል። ሪያል ማድሪድ እ.አ.አ በ2021/21 የውድድር ዓመት ብራሂም ዲያዝ ወደ ኤሲ ሚላን በውሰት ማምራቱን ይፋ አደረገ። ዲያዝ ሚላን እ.አ.አ መስከረም 27 ቀን 2020 ክሮቶኔን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ የመጀመሪያ ግቡን ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ ግንቦት 2021 ኤሲ ሚላን ጁቬንቱስን 3 ለ 0 ሲያሸንፍ ያስቆጠረው ግብም ተጠቃሽ ነው። ዲያዝ በኤሲ ሚላን የውሰት ውሉ ሲያበቃ በድጋሚ ለሁለት ዓመታት በውሰት የሚቆይበት ስምምነት ሪያል ማድሪድ ከጣልያኑ ክለብ ጋር የተፈራረመ ሲሆን፤ ውሉ ሚላን ተጫዋቹን የማቆየት መብት ሰጥቶታል። እ.አ.አ መስከረም 15 ቀን 2021 ኤሲ ሚላን በሻምፒዮንስ ሊጉ የ3 ለ 2 ሽንፈት ሲያስተናግድ የመጀመሪያ የአውሮፓ መድረክ ግቡን አስቆጥሯል። በ2023 ኤሲ ሚላን ቶተንሃም ሆትስፐርስን በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ጥሎ ማለፍ 1 ለ 0 ሲያሽንፍ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ በ2023 ሰኔ ወር ላይ ሪያል ማድሪድ ዲያዝ ከኤሲ ሚላን የሶስት ዓመታት የውሰት ቆይታ በኋላ ወደ ክለቡ መመለሱን አሳውቋል። ተጫዋቹ በኤሲ ሚላን ቆይታው 91 ጨዋታዎችን አድርጎ 13 ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ዲያዝ ወደ ሪያል ማድሪድ ከተመለሰ በኋላ ኮንትራቱን እስከ 2027 አራዝሟል። እ.አ.አ መስከረም 27 ቀን 2023 ወደ ክለቡ ከተመለሰ በኋላ ሪያል ማድሪድ ላስ ፓልማስን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ ግብ አስቆጥሯል። የክንፍ መስመር ተጫዋቹ ሪያል ማድሪድ በሀገር ውስጥ እና በአውሮፓ መድረክ በሚያደርጋቸው ጨዋታዎች ላይ ግብ በማስቆጠር እና ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል። ዲያዝ እስከ አሁን ለሪያል ማድሪድ ባደረጋቸው 129 ጨዋታዎች 20 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከነዚህም ውስጥ 13ቱ በላሊጋው ያስቆጠራቸው ናቸው። ከክለብ ወጣ ስንል የተጫዋቹን የብሔራዊ ቡድን ቆይታ እናገኛለን። ዲያዝ በታዳጊነቱ በተለያዩ የእድሜ እርከኖች ለስፔን ወጣት ቡድኖች ተጫውቷል። እ.አ.አ በ2016/17 የውድድር ዘመን ለስፔን ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በ16 ዓመቱ ተሰልፎ መጫወት ችሏል። በተለይም አዘርባጃን እ.አ.አ በ2017 ባዘጋጀችው 15ኛው የአውሮፓ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ላይ ያሳየው ድንቅ ብቃት አድናቆት አስችሮታል። በዚያ ቀጥለው በነበሩ ዓመታትም ለስፔን ከ19 እና ከ21 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድኖች ተጫውቷል። ብራሂም ዲያዝ በስፔን ታዳጊና ወጣት ቡድኖች ላይ በአጠቃላይ 28 ጨዋታዎችን አድርጎ ስድስት ግቦችን አስቆጥሯል። የስፔን ታዋቂ የስፖርት ጋዜጣ ማርካ እ.አ.አ ጥር 23 ቀን 2023 ለሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን መጫወት ማቀዱን የሚመለከት ዘገባ ይዞ ወጥቷል። ከዜግነቱ ጋር በተያያዘ ያሉ አንዳንድ የአስተደዳር ጉዳዮች በወቅቱ መፍትሄ አግኝተዋል። ይሁንና ኮትዲቯር እ.አ.አ በ2023 ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሞሮኮው አሰልጣኝ ዋሊድ ሬግራጉዊ ከተጫዋቹ ጋር በተደረገ የቅድሚያ ስምምነት ለተጫዋቹ ጥሪ አልተደረገለትም። ዲያዝ እ.አ.አ መጋቢት 10 ቀን 2024 ለሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለሀገሪቷ ብሔራዊ መጫወት እንደሚፈልግ በይፋ ማሳወቁን ማርካ በወቅቱ ዘግቧል። ጥያቄውም ተቀባይነት አገኘ። በወቅቱ የሞሮኮ አሰልጣኝ ዋሊድ ሬግራጉዊ ብሔራዊ ቡድኑ ከአንጎላ እና ሞሪታኒያ ጋር ለነበረበት የወዳጅነት ጨዋታ ለዲያዝ ጥሪ አድርገውለታል። እ.አ.አ መጋቢት 22 ቀን 2024 ሞሮኮ አንጎላን 1 ለ 0 ባሸነፈችበት ጨዋታ ለብሔራዊ ቡድኑ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። እ.አ.አ ጥቅምት 6 ቀን 2024 ሞሮኮ ለ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከጋቦን ጋር ባደረገችው ጨዋታ 4 ለ 1 ስታሸንፍ የመጀመሪያ ግቡን ለሞሮኮ ማስቆጠር ቻለ። እ.አ.አ ሕዳር 15 ቀን 2024 ሞሮኮ በማጣሪያው ጋቦንን 5 ለ 1 ስትረታ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ማሳረፍ ችሏል። ከሶስት ቀናት በኋላ ሞሮኮ ከሌሴቶ ጋር ባደረገችው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታ 7 ለ 0 ስታሸንፍ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር በሀገሩ ማልያ የመጀመሪያ ሀትሪኩን ሰርቷል። እ.አ.አ ጥቅምት 2025 ሞሮኮ ራባት ላይ ኮንጎ ሪፐብሊክን 1 ለ 0 በማሸነፍ በስፔን ከዚህ ቀደም በብሔራዊ ቡድን ደረጃ ተይዞ የነበረውን 15 ተከታታይ ጨዋታዎችን የማሸነፍ ክብረ ወሰን በመስበር ወደ 16 ማድረስ ችላለች። በዚህ ታሪካዊ ጨዋታ ላይ ዲያዝ ተሰልፎ ተጫውቷል። የሞሮኮ ተከታታይ የማሸነፍ ጉዞ 19 ጨዋታዎች ደርሶ የነበረ ሲሆን በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከማሊ ጋር አንድ አቻ ስትለያይ አብቅቷል። ሞሮኮ ለ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በማጣሪያ ብታልፍም አስቀድማ ውድድሩን እንድታዘጋጅ እድል አግኝታ የነበረው ጊኒ በዝግጅት ማነስ ምክንያት በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ከሁለት ዓመት በፊት አዘጋጅነቷ ተነጥቆ ለሞሮኮ ተሰጥቷል። ሞሮኮ የዘንድሮውን ውድድር በደማቅ ሁኔታ እያካሄደች ትገኛለች። በውድድሩ ላይ ጎልተው ከታዩ ተጫዋቾች መካከል ብራሂም ዲያዝ ተጠቃሽ ነው። በአፍሪካ ዋንጫው እስከ አሁን ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። በተሰለፈባቸው በእያንዳዱ ጨዋታዎች ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ለሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን በአምስት የአፍሪካ ዋንጫ ተከታታይ ጨዋታዎች ግብ ያስቆጠረ የመጀመሪያው ተጫዋች በመሆን አዲስ ታሪክ ጽፏል። ሞሮኮ በሩብ ፍጻሜው ማሊን 2 ለ 0 ስታሸንፍ የመጀመሪያውን ጎል አስቆጥሯል። ሀገሩ ወደ ግማሽ ፍጻሜ እንድታልፍ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱንም እየመራ ይገኛል። ሞሮኮ በዚሁ ግስጋሴዋ ከቀጠለች ዲያዝ የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ እና ኮከብ ተጫዋች የመሆን እድሉ ሰፊ ነው። ሞሮኮ በግማሽ ፍጻሜው ከናይጄሪያ ጋር ረቡዕ ጥር 6 ቀን 2018 ዓ.ም በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ታደርጋለች። ዲያዝ በዚህ ጨዋታ ላይ ልዩነት ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል። አንዳንድ የእግር ኳስ ተንታኞች ብራሂም ዲያዝ እ.አ.አ በ2026 ወጥነት ያለው ብቃት ማሳየት ከቻለ የአፍሪካ ኮከብ ተጫዋችነት ሽልማቱን የሚወስድበት የለም እያሉ ይገኛሉ። ሞሮኳውያን በተጫዋቹ ፍቅር ልባቸው ከንፏል። በየጨዋታው ዲያዝ ዲያዝ እያሉ ከፍተኛ ድጋፍ እና ሙገሳ እየሰጡት ይገኛሉ። እሱም በድንቅ ብቃቱ ምላሽ እየሰጣቸው ነው። በተወለደበት ማላጋ ከተማ የጀመረው የእግር ኳስ ሕይወት በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የበለጠ አብቧል። የሞሮኮው አዲሱ ኮከብ ብራሂም ዲያዝ ቀጣይ የእግር ኳስ ሕይወት በስኬት እና በድል የደመቀ እንደሚሆን ከአሁኑ ድንቅ ብቃቱ ተነስቶ መናገር ይቻላል።
በዓለም ሀገር አቋራጭ ሻምፒዮና ሁለተኛ በመሆን ያጠናቀቀው የኢትዮጵያ ልዑክ አቀባበል ተደረገለት
Jan 13, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ በአሜሪካ ፍሎሪዳ በተካሄደው 46ኛው የዓለም ሀገር አቋራጭ ሻምፒዮና የተሳተፈው የኢትዮጵያ ልዑክ ቡድን አቀባበል ተደርጎለታል። ልዑካን ቡድኑ ዛሬ ማለዳ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ሲደርስ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ ፣ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ መኪዩ መሐመድ፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት፣ የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ፕሬዚዳንት አሸብር ወልደጊዮርጊስ (ዶ/ር) እና ሌሎች አመራሮች አቀባበል አድርገውታል ። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በሶስት የወርቅ፣ ሁለት የብር እና ሁለት የነሐስ በአጠቃላይ ሰባት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ኬንያን ተከትላ ከዓለም ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች።