ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
በፕሪሚየር ሊጉ ኤቨርተን አስቶንቪላን አሸነፈ
Jan 18, 2026 42
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ22ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ኤቨርተን አስቶንቪላን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቲዬርኖ ባሪ በ59ኛው ደቂቃ ላይ የማሸነፊያ ግቡን አስቆጥሯል። በጨዋታው ላይ አስቶንቪላ ብልጫ ቢወስድም ግብ ማስቆጠር አልቻለም። ኤቨርተን የመከላከል እና የመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴው አሸናፊ አድርጎታል። በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ድሉን ያስመዘገበው ኤቨርተን በ32 ነጥብ ከ12ኛ ደረጃ ወደ 10ኛ ከፍ ብሏል። ኤቨርተን ከ10 ዓመታት በኋላ አስቶንቪላን በሊጉ ማሸነፍ ችሏል። በአንጻሩ በሊጉ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አስቶንቪላ በ43 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። አስቶንቪላ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ዝቅ የማድረግ እድሉን ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ዛሬ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ዎልቭስ ከኒውካስትል ዩናይትድ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የ22ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ-ግብር በብራይተን እና ቦርንማውዝ መካከል ነገ ይደረጋል።
አስቶንቪላ ከኤቨርተን ጋር ይጫወታል
Jan 18, 2026 76
አዲስ አበባ፤ ጥር 10/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ22ኛ ሳምንት ሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ አስቶንቪላ ከኤቨርተን በቪላ ፓርክ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አስቶንቪላ በ43 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኤቨርተን በ29 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ክለቦች በሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ81ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 80 ጨዋታዎች አስቶንቪላ 40 ጊዜ ድል ሲቀናው ኤቨርተን በ22ቱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ 18 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በ80 ጨዋታዎች አስቶንቪላ 102 ግቦችን ሲያስቆጥር ኤቨርተን 79 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች በነበራቸው ግንኙነት አስቶንቪላ ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ኤቨርተን ለመጨረሻ ጊዜ አስቶንቪላን በሊጉ ያሸነፈው እ.አ.አ ማርች 1 2016 ሲሆን በወቅቱ የ3 ለ 1 ድል ተቀዳጅቷል። ቡድኖቹ በዘንድሮው የውድድር ዓመት በአራተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ባደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። አስቶንቪላ ካሸነፈ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ዝቅ ያደርጋል። ኤቨርተን ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ቶኒ ሃሪንግተን ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌላኛው መርሃ ግብር ዎልቭስ ከኒውካስትል ዩናይትድ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የአፍሪካ ዋንጫን ማን ያነሳል? ሴኔጋል ወይስ አዘጋጇ ሞሮኮ?
Jan 18, 2026 389
አዲስ አበባ፤ ጥር 10/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የፍጻሜ መርሃ ግብር ሴኔጋል እና ሞሮኮ ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አሸናፊው ሀገር ከዋንጫው በተጨማሪ 10 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ወደ ካዝናው ያስገባል። የብሄራዊ ቡድኖቹ ጨዋታ ምሽት አራት ላይ በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ይካሄዳል። ጨዋታው የእግር ኳስ አፍቃሪያንን ትኩረት ስቧል። በግማሽ ፍጻሜው ሴኔጋል ግብጽን፣ ሞሮኮ ናይጄሪያን በማሸነፍ ለዋንጫው ፍልሚያ ቀርበዋል። የፍጻሜ ተፋላሚ ሀገራቱ በዘንድሮ የአፍሪካ ዋንጫ ሽንፈት አላስተናገዱም። ሴኔጋል በውድድሩ ላይ እስከ አሁን ስድስት ጨዋታዎችን አድርጋ አምስቱን ስታሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይታለች። በጨዋታዎቹ ላይ 12 ግቦችን ስታስቆጥር ሁለት ግቦችን አስተናግዳለች። አዘጋጇ ሞሮኮ ካደረገቻቸው ስድስት ጨዋታዎች መካከል አራቱን ስታሸንፍ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥታለች። በጨዋታዎቹ ላይ ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ የተቆጠረባት አንድ ጎል ብቻ ነው። ሞሮኮ በውድድሩ ላይ ዝቅተኛ የግብ መጠን የተቆጠረባት ሀገር ናት። ሴኔጋል እና ሞሮኮ በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም በውድድር እና በወዳጅነት ጨዋታዎች በአጠቃላይ 33 ጊዜ ተገናኝተዋል። ሞሮኮ 18 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዛለች። ሴኔጋል በሰባቱ ስታሸንፍ በቀሪ ስድስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ሞሮኮ በጨዋታዎቹ ላይ 41 ግቦችን ስታስቆጥር፣ ሴኔጋል 17 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ሁለቱ ሀገራት ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ ኦገስት 2025 በኬንያ፣ ዩጋንዳ እና ታንዛንያ ጣምራ አዘጋጅነት በተካሄደው ስምንተኛው የአፍሪካ ሀገራት ሻምፒዮና (ቻን)ላይ ነበር። በግማሽ ፍጻሜው ተገናኝተው ሞሮኮ ሴኔጋልን በመለያ ምት 4 ለ 2 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፋለች። ሞሮኮ በፍጻሜው ማዳጋስካርን በመርታት ዋንጫውን አንስታለች። ሀገራቱን በዘንድሮው ውድድር ከሚያመሳስላቸው ጉዳዮች አንዱ ከጨዋታ ጨዋታ ይበልጥ ጥንካሬያቸውን እና አቅማቸውን እያሳደጉ መምጣታቸው ነው። ሴኔጋል ጠንካራ የመከላከል አደረጃጀት፣ ማጥቃት እና መከላከል ላይ ተመጣጣኝ ሚዛን በመስራት የሚጫወተው የአማካይ ክፍል፣ የማጥቃት አቅም እና በድንቅ ብቃት ላይ የሚገኘው ግብ ጠባቂ ኤድዋርድ ሜንዲ የጥንካሬዎቿ ማሳያ ናቸው። በተወሰኑ ተጫዋቾች ላይ ጥገኛ መሆን እና ለፈጣን መልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴዎች ተጋላጭ መሆን እንደ ድክመት ይነሳል። አዘጋጇ ሞሮኮ ቅርጹን የጠበቀ እና በቀላሉ ሰብሮ መግባት የማይቻል የተከላካይ ክፍል ገንብታለች። የቀኝ እና ግራ መስመር ተመላላሽ ተጫዋቾች የማጥቃት ብቃት፣ በክህሎት የተሞላው የአማካይ ክፍል እና ከተለያዩ አማራጮች ግብ ማስቆጠር መቻሏ እንደ ጥንካሬ የሚነሳ ነው። በጣም ጥንቃቄ የታከለበት የሞሮኮ የኳስ ቅብብል በጣም ተጭነው እና ፍሰትን ለማበላሸት በሚጫወቱ የተጋጣሚ ቡድኖች ለአደጋ የተጋለጠ ሲሆን ይህም የማጥቃት አቅምን ሲቀንስ ታይቷል። ሞሮኮ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ በጥልቀት የሚጫወቱ ቡድኖችን አስከፍታ ለመጫወት ስትቸገር ለመመልከት ተችሏል። በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ሁለት ግቦችን በማስቆጠር እና ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ ያቀበለው ሳዲዮ ማኔ የሴኔጋል ቁልፍ ተጫዋች ነው። አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የውድድሩ ክስተት የሆነው የሞሮኮው ብራሂም ዲያዝ በጨዋታው ላይ ልዩነት ይፈጥራሉ ተብለው ከሚጠበቁ ተጫዋቾች መካከል ይገኝበታል። ጨዋታው በታክቲክ የታጠረ እና ጥንቃቄ የተሞላበት ሊሆን እንደሚችል ይጠበቃል። ሴኔጋል እ.አ.አ በ2022 በካሜሮን አስተናጋጅነት የተካሄደውን 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ያነሳች ሲሆን ውድድሩን ለሁለተኛ ጊዜ ለማሸነፍ ትጫወታለች። ተጋጣሚዋ ሞሮኮ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1976 ባዘጋጀችው 10ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ብቸኛ አህጉራዊ ድሏን ማሳካት ችላለች። ከ50 ዓመታት ራሷ ያዘጋጀችውን ዋንጫ ለመውሰድ ትፋለማለች። አሸናፊው ሀገር ከዋንጫው በተጨማሪ የ10 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ያገኛል። ይህም ከ34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የ43 በመቶ ብልጫ እንዳለው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል። ሁለተኛ የሚወጣው ሀገር የአራት ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ያገኛል። አጠቃላይ ለተሳታፊ ሀገራት የ32 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ይበረከታል። ከታህሳስ 12 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በሞሮኮ አስተናጋጅነት ሲካሄድ የቆየው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ ይጠናቀቃል።
የሊጉ መሪ አርሰናል እና ኖቲንግሃም ፎረስት አቻ ተለያዩ
Jan 17, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ22ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ኖቲንግሃም ፎረስት እና አርሰናል ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ማምሻውን በሲቲ ግራውንድ ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ ብልጫ ወስዶ የተጫወተው አርሰናል ያገኛቸውን የግብ እድሎች አለመጠቀሙ ሶስት ነጥብ እንዳያገኝ አድርጎታል። በመጀመሪያው አጋማሽ ጋብርኤል ማርቲኔሊ የሳተው ግልጽ የግብ እድል ተጠቃሽ ነው። ተጋጣሚው ኖቲንግሃም ፎረስት ወደ ኋላ አፈግፍጎ የመከላከል እና የመልሶ ማጥቃት ስልት ይዞ በመግባት ግብ ሳይቆጠርበት ወጥቷል። ውጤቱን ተከትሎ የሊጉ መሪ አርሰናል ነጥቡን ወደ 50 ከፍ አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ አርሰናል ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሰባት ከፍ አድርጓል። አርሰናል ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ያላሸነፈ ሲሆን ግብም ማስቆጠር አልቻለም። ኖቲንግሃም ፎረስት በሊጉ በ22 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ናይጄሪያ ግብጽን በማሸነፍ በአፍሪካ ዋንጫው ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቀቀች
Jan 17, 2026 74
አዲስ አበባ፤ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የደረጃ ጨዋታ ናይጄሪያ ግብጽን በመለያ ምት አሸንፋለች። ማምሻውን በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም የተደረገው ጨዋታ በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ግብ አቻ ተጠናቋል። ጨዋታው ቀጥታ ወደ መለያ ምት አምርቷል።በዚህም ናይጄሪያ 4 ለ 2 በማሸነፍ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። የነሐስ ሜዳሊያም አግኝታለች። ግብጽ አራተኛ በመሆን ጨርሳለች። በጨዋታው ናይጄሪያ የግብ እድል በመፍጠር፣ ግብጽ በኳስ ቁጥጥር የተሻሉ ነበሩ። ናይጄሪያ ሶስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አንስታለች። ግብጽ ውድድሩን ሰባት ጊዜ በማሸነፍ ስኬታማዋ ሀገር ናት።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከአዳማ ከተማ ጋር አቻ ተለያየ
Jan 17, 2026 72
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ- ግብር ሲዳማ ቡና እና አዳማ ከተማ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ መስፍን ታፈሰ ለሲዳማ ቡና ግቦቹን አስቆጥሯል። አቡበከር ሳኒ እና ሙጂብ ቃሲም ለአዳማ ከተማ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ነጥቡን ወደ 30 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ነገሌ አርሲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማስፋት እድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል። አዳማ ከተማ በ23 ነጥብ 7ኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታውን ተከትሎ የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ16ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከጥር 12 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እንደሚካሄዱ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
በፕሪሚየር ሊጉ ቼልሲ ድል ሲቀናው ሊቨርፑል ነጥብ ጥሏል
Jan 17, 2026 65
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 22ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማምሻውን አምስት ጨዋታዎች ተደርገዋል። በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቼልሲ ብሬንትፎርድን 2 ለ 0 አሸንፏል። ጆአኦ ፔድሮ በጨዋታ እና ኮል ፓልመር በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ቼልሲ በ34 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ብሬንትፎርድ በ33 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሊቨርፑል ከበርንሌይ አንድ አቻ ተለያይቷል። በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፍሎሪያን ዊትዝ ለሊቨርፑል፣ ማርከስ ኤድዋርድስ ለበርንሌይ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሊቨርፑል በጨዋታው ላይ ያገኘውን የፍጹም ቅጣት ምት አማካዩ ዶምኒክ ስቦዝላይ ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ሊቨርፑል በ36 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ሲይዝ በርንሌይ በ14 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ሰንደርላንድ ክሪስታል ፓላስን ፣ ዌስትሃም ዩናይትድ ቶተንሃም ሆትስፐርስን በተመሳሳይ 2 ለ 1 አሸንፈዋል። ሊድስ ዩናይትድ ፉልሃምን 1 ለ 0 ረቷል። በአሁኑ ሰዓት የሊጉ መሪ አርሰናል ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር ጨዋታውን እያደረገ ይገኛል።
በክልሉ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የስፖርት ማዘውተሪያ ልማት ስራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ነው
Jan 17, 2026 108
ዲላ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ) ፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የስፖርት ማዘውተሪያ ልማት ስራዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑ ተገለጸ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የታዳጊዎች ምዘናና የባህል ስፖርት ውድድር ፌስቲቫል ዛሬ በዲላ ከተማ መካሄድ ጀምሯል። በመርሀ ግብሩ መክፈቻ ላይ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) እንዳሉት በክልሉ ተሰጥኦ ያላቸው ታዳጊዎች ወደ ስፖርት መምጣት እንዲችሉ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። ከነዚህ ተግባራት መካከል ተተኪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ የስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታ ስራ ዋናው መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም ከከተሞች ኮሪደር ልማት ጋር በማስተሳሰር የስፖርት ማዘወተሪያ ስፍራ ልማት እየተከናወነ መሆኑን አንስተው ይህም ተተኪ ስፖርተኞች ለማፍራት ድርሻው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል። ዛሬ የተጀመረው ታዳጊዎች ምዘናና የባህል ስፖርት ውድድር ተሳታፊዎችም ስፖርታዊ ጨዋነትን በመላበስ ወንድማማችነትን እና እህትማማችነትን ማጠናከር እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ውድድሩ የታዳጊ ወጣቶችን አቅም በማጎልበት ብቁና ተወዳዳሪ የሆኑ ተተኪ ስፖርተኞችን ማፍራት ዓላማ ያደረገ ነው ያሉት ደግሞ የክልሉ ባህልና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኦላዶ ኦሎ ናቸው። ፌስቲቫሉ ከውድድርና ምዘና ባለፈ የክልሉ ህብረ ብሔራዊነትና ቱባ ባህሎች በአደባባይ የሚንጸባረቅበትና አንድነት የሚጎላበት መድረክ ነው ብለዋል። በውድድሩ ላይ በክልሉ ከሚገኙ 12 የዞንና ሶስት ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ታዳጊ ስፖርተኞች የሚሳተፉ ሲሆን በተለይ በእግር ኳስ ረገድ ክልሉን ወክለው በሃገር ደረጃ የሚሳተፉ 33 ታዳጊዎች ምልመላ እንደሚከናወን አንስተዋል። ውድድሩ ከ11 በላይ ባህላዊና ዘመናዊ ስፖርቶችን በሁለቱም ጾታዎች ያቀፈ መሆኑን ጠቅሰው ከ1 ሺህ 600 በላይ የስፖርት ልዑካን እንደሚሳተፉም ተናግረዋል። የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ መስፍን ደምሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፌስቲቨሉ በከተማው መካሄዱ የስፖርት እንቅስቃሴን ከማነቃቃት ባለፈ የከተማዋን ገጽታ ለመገንባት ድርሻው የጎላ ነው ብለዋል። በተለይ በከተማው የሚገኙ ታዳጊ ስፖርተኞች በውድድሩ ከመሳተፍ ባለፈ ልምድ በመቅሰም ተወዳዳሪነታቸውን የሚያጠናክሩበት መልካም አጋጠሚ መሆኑን አንስተዋል። በመርሃ ግብሩ ማስጀመሪያ ላይ የክልል፣ የዞንና የከተማ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች፣ የሁሉም መዋቅሮች የስፖርት ልዑካንና የስፖርቱ ቤተሰብ ተሳተፊ ሆነዋል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ከስድስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመለሰ
Jan 17, 2026 57
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስ ድሬዳዋ ከተማን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አምበሉ አቤል ያለው በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር፤ ሀብታሙ ጉልላት እና ፍጹም ጥላሁን ደግሞ ቀሪዎቹን ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የድሬዳዋ ከተማው አማካይ ሄኖክ ሀሰን በ22ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ይህም በጨዋታው ላይ ተጽእኖ አሳድሯል። ከስድስት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ቅዱስ ጊዮርጊስ፤ በ22 ነጥብ ደረጃውን ከ10ኛ ወደ 7ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱም ስድስተኛ ድሉን አሳክቷል። በአንጻሩ በሊጉ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ18 ነጥብ ከነበረበት 12ኛ ደረጃ ወደ 13ኛ ዝቅ ብሏል።
በተጠባቂው የደርቢ ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ ማንችስተር ሲቲን አሸነፈ
Jan 17, 2026 100
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 22ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ-ግብር ማንችስተር ዩናይትድ ማንችስተር ሲቲን 2 ለ 0 አሸንፏል። በኦልድትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብራያን ምቡዌሞ በ65ኛውና ፓትሪክ ዶርጉ በ76ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ምቡዌሞ በዩናይትድ ማልያ ሰባተኛ የሊግ ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ላይ ማንችስተር ዩናይትድ ብልጫ ወስዶ የተጫወተ ሲሆን፤ ተጨማሪ ግቦችን የማስቆጠር እድሎችን ቢያገኝም ሳይጠቀምበት ቀርቷል። የዓለም አይኖች ያረፉበት ተጠባቂው የማንችስተር ደርቢ ማንችስተር ሲቲ ደካማ የማጥቃት እንቅስቃሴ አድርጓል። ይህን ተከትሎም 198ኛው የማንችስተር ደርቢ በማንችስተር ዩናይትድ አሸናፊነት ተጠናቅቋል። በሊጉ 10ኛ ድሉን ያስመዘገበው ዩናይትድ በ35 ነጥብ ደረጃውን ከሰባተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ማንችስተር ሲቲ በ43 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማጥበብ እድል አምክኗል። ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች አላሻነፈም። የሊጉ መሪ አርሰናል ዛሬ ማምሻውን ኖቲንግሃም ፎረስት ካሸነፈ ከሲቲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ዘጠኝ ከፍ ያደርጋል።
ኢትዮጵያ ቡና እና ሐዋሳ ከተማ ነጥብ ተጋሩ
Jan 17, 2026 55
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና እና ሐዋሳ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ናይጄሪያዊው ዲቫይን ዋቹኩዋ በ38ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ኢትዮጵያ ቡና መሪ ሆኗል። ጌታነህ ከበደ በ93ኛው ደቂቃ ለሐዋሳ ከተማ የአቻነቷን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎም ኢትዮጵያ ቡና በ19 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ሐዋሳ ከተማ በ25 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ ማድረግ ችሏል።
ለስፖርቱ ዘርፍ እድገት የማዘውተሪያ ስፍራዎች ግንባታ እና የታዳጊዎች ስልጠና ላይ በትኩረት እየተሰራ ነው
Jan 17, 2026 130
አሶሳ፤ ጥር 9/2018(ኢዜአ)፦ ለስፖርቱ ዘርፍ እድገት የማዘውተሪያ ስፍራዎች ግንባታ እና የታዳጊዎች ስልጠና ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስፖርት ኮሚሽን አስታወቀ። በክልሉ ከዛሬ ጀምሮ ለተከታታይ 7 ቀናት የሚካሄድ ከ15 ዓመት በታች የታዳጊ ፕሮጀክት የምዘና ውድድር በአሶሳ ከተማ ተጀምሯል። በመርሃ ግብሩ ማስጀመሪያ ላይ በመገኘት መልእክት ያስተላለፉት የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ኢብራሂም ሀጂ መንሱር፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ ታዳጊዎች ላይ መሠረት ያደረገ የስፖርት ፖሊሲ በመተግበር ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ ለስፖርቱ እድገትና ማንሰራራት የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን በማንሳት በዛሬው እለት የተጀመረው ውድድርም የዚሁ ማሳያ ነው ብለዋል። የውድድሩ ዓላማ በሀገር አቀፍ ደረጃ ክልሉን የሚወክሉ ስፖርተኞችን ለመመልመል እና ታዳጊዎች የወሰዱትን ስልጠና ለመመዘን እንደሆነ ገልጸዋል። ለስፖርቱ ዘርፍ እድገት የማዘውተሪያ ስፍራዎች ግንባታ እና የታዳጊዎች ስልጠና ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸው ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የአሶሳ ከተማ ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ፍቃዱ በየነ፤ በክልሉ እየተነቃቃ ላለው የስፖርት ዘርፍ ውጤታማነት የተለያዩ የስፖርት መሠረተ ልማቶች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ከ15 ዓመት በታች የታዳጊ ፕሮጀክት የምዘና ውድድር በእግርኳስ፣ አትሌቲክስ፤ ቮሊ ቦል፣ ቦክስ፣ ወርልድ ቴኳንዶን ጨምር በ9 የስፖርት ዓይነቶች የሚካሄድ መሆኑ ታውቋል።
መቻል ወደ ድል ተመልሷል
Jan 17, 2026 53
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር መቻል አርባ ምንጭ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቸርነት ጉግሳ በ68ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት እና ዩጋንዳዊው ቻርልስ ሙሲጌ በ91ኛው ደቂቃ በጨዋታ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ከሦስት ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው መቻል በ23 ነጥብ ደረጃውን ከሰባተኛ ወደ ስድስተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉም ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባ ምንጭ ከተማ በስምንት ነጥብ በደረጃ ሠንጠረዡ ግርጌ ላይ ተቀምጧል። አርባ ምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከአዳማ ከተማ ጋር ይጫወታል
Jan 17, 2026 71
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዛሬ በሚደረጉ አራት ጨዋታዎች ይጠናቀቃል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከሲዳማ ቡና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዳማ ከተማ በሊጉ 14 ጨዋታዎችን አድርጎ በአምስቱ ድል ሲቀናው በሁለቱ ተሸንፏል። በቀሪ ሰባት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ22 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ሲዳማ ቡና በሊጉ ካከናወናቸው 14 ጨዋታዎች መካከል ስምንቱን ሲያሸንፍ የተሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 18 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ ስድስት ግቦች ተቆጥረውበታል። ሊጉን በ29 ነጥብ እየመራ ነው። ሁለቱ ቡድኖች በ14ኛ ሳምንት አቻ ከተለያዩባቸው መርሐ-ግብሮች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ሲዳማ ቡና ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። አዳማ ከተማ ከሁለት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ኢትዮጵያ ቡና ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው 14 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ያሸነፈው ኢትዮጵያ ቡና በስድስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በ14ቱ ጨዋታዎች ላይ 13 ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎችን አስተናግዷል። ኢትዮጵያ ቡና በ18 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሃዋሳ ከተማ በበኩሉ በ14 ጨዋታዎች ሰባቱን አሸንፎ በአራቱ ሽንፈት አስተናግዶ በሶስቱ አቻ ወጥቷል። 15 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ዘጠኝ ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሃዋሳ ከተማ በ24 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱም ቡድኖች በአሸናፊነት ለመቀጠል የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ19 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ በ18 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለፉት ስድስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከመቻል በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አርባምንጭ ከተማ በስምንት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። መቻል በ20 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው። መቻል ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ጨዋታው አርባምንጭ ከተማ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ፣ መቻል ወደ ድል መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
በአፍሪካ ዋንጫ ግብጽ እና ናይጄሪያ ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ይጫወታሉ
Jan 17, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የደረጃ ጨዋታ ዛሬ በግብጽ እና ናይጄሪያ መካከል ይደረጋል። ጨዋታው ምሽት አንድ ሰዓት ላይ በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም ይካሄዳል። በግማሽ ፍጻሜው ግብጽ በሴኔጋል፣ ናይጄሪያ በሞሮኮ ሽንፈት አስተናግደዋል። የዓለም አይኖች ያረፉበት ተጠባቂው የማንችስተር ደርቢ የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከአዳማ ከተማ ጋር ይጫወታል ግብጽ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ እስከ አሁን ባደረገቻቸው ስድስት ጨዋታዎች አራቱን ስታሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፋለች። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይታለች። በጨዋታዎቹ ላይ ስምንት ግቦችን ስታስቆጥር አምስት ጎሎችን አስተናግዳለች። ተጋጣሚዋ ናይጄሪያ ከስድስት ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ስታሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፋለች። 14 ግቦችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ አራት ጎሎች ተቆጥሮባታል። ናይጄሪያው በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ በርካታ ግቦችን ያስቆጠረች ሀገር ናት። ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለ10ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ዘጠኝ ጨዋታዎች ናይጄሪያ በአምስቱ ድል ሲቀናት ግብጽ ሁለት ጊዜ አሸንፋለች። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በጨዋታዎቹ ላይ ሁለቱም ሀገራት በተመሳሳይ 11 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሀገራቱ ለመጀመሪያ ጊዜ በአህጉራዊው መድረክ የተገናኙት ጋና እ.አ.አ በ1963 ባዘጋጀችው አራተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በወቅቱ በምድብ ሁለት ተገናኝተው ግብጽ 6 ለ 3 አሸንፋለች። ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት ካሜሮን እ.አ.አ በ2022 ባስተናገደችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው። በምድብ አራት ባደረጉት ጨዋታ ናይጄሪያ በኬሌቺ ኢናቺዮ ግብ ግብጽን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ናይጄሪያ የአፍሪካ ዋንጫን ሶስት ጊዜ ስታሸነፍ ግብጽ ሰባት ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት የውድድሩ ስኬታማ ሀገር ናት። የአፍሪካ እግር ኳስ ኃያላን የሆኑት ሁለቱ ሀገራት በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ለፍጻሜ ባይደርሱም ሶስተኛ ደረጃን ይዞ በአዎንታዊ መልኩ ውድድሩን ለማጠናቀቅ ይፋለማሉ። የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የፍጻሜ ጨዋታ ነገ በሴኔጋል እና አዘጋጇ ሞሮኮ መካከል ይደረጋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የዓለም አይኖች ያረፉበት ተጠባቂው የማንችስተር ደርቢ
Jan 17, 2026 127
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ22ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል። ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ማንችስተር ዩናይትድ ከማንችስተር ሲቲ በኦልድትራፎርድ ስታዲየም የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ማንችስተር ዩናይትድ በ32 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ማንችስተር ሲቲ በ43 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ሁለቱ ክለቦች በሁሉም ውድድሮች ሲገናኙ የአሁኑ ለ198ኛ ጊዜ ነው። ቡድኖቹ ከዚህ በፊት ባደረጓቸው 197 ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ 80 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ 63 ጊዜ ሲያሸንፍ 54 ጊዜ ነጥብ ተጋርተዋል። በፕሪሚየር ሊጉ 57 ጊዜ ተገናኝተው ማንችስተር ዩናይትድ 26 ጊዜ ሲያሸንፍ ሲቲ በ21ዱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ 10 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ማንችስተር ሲቲ ሶስቱን ሲያሸንፍ ማንችስተር ዩናይትድ አንድ ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። ማንችስተር ዩናይትድ እና ማንችስተር ሲቲ የአንድ ከተማ ባላንጣ ቡድኖች ናቸው። ክለቦቹ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ1881 ነበር። በዚህ ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ 3 ለ 0 አሸንፏል። ቡድኖቹ ከመጀመሪያ ጨዋታቸው አንስቶ ለ145 ዓመታት የቆየ ፉክክር በእንግሊዝ እና በአውሮፓ መድረክ አድርገዋል። ማንችስተር ዩናይትድ የሊጉን ዋንጫ 20 ጊዜ በማንሳት የበላይነቱን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ 10 ጊዜ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ሆኗል። ማንችስተር ዩናይትድ በጊዜያዊ አሰልጣኙ ማይክል ካሪክ እየተመራ ወደ ሜዳ ይገባል። ሁለቱ ክለቦች በሊጉ በመጀመሪያ ዙር ባደረጉት ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ 3 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ክለቦቹ በተመሳሳይ ባለፉት ሶስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። የ47 ዓመቱ የማንችስተር ከተማ ተወላጅ አንቶኒ ቴይለር ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመራሉ። በሌላ በኩል የሊጉ መሪ አርሰናል ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር በሲቲ ግራውንድ ስታዲየም ጨዋታውን ያደርጋል። ሊቨርፑል ከበርንሌይ፣ ቼልሲ ከብሬንትፎርድ፣ ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከዌስትሃም ዩናይትድ፣ ሰንደርላንድ ከክሪስታል ፓላስ እና ሊድስ ዩናይትድ ከፉልሃም በተመሳሳይ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰበትን ድል አስመዘገበ
Jan 16, 2026 71
አዲስ አበባ፤ ጥር 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ እዮብ ገብረማርያም እና ሀሰን ሁሴን የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቢኒያም ካሳሁን ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ25 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ17 ነጥብ ከነበረበት 12ኛ ደረጃ ወደ 13ኛ ዝቅ ብሏል።
ሀዲያ ሆሳዕና ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Jan 16, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ጥር 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሀዲያ ሆሳዕና ምድረገነት ሽሬን 3 ለ 1 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኤልያስ አሕመድ እና ሱራፌል ተመስገን በጨዋታ፣ ብሩክ በየነ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ተካልኝ ደጀኔ ለምድረገነት ሽሬ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሀዲያ ሆሳዕና በ20 ነጥብ ደረጃውን ከ15ኛ ወደ 9ኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ አምስተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ምድረገነት ሽሬ በ17 ነጥብ ከነበረበት 13ኛ ደረጃ ወደ 14ኛ ዝቅ ብሏል።
ነጌሌ አርሲ እና ወላይታ ድቻ አቻ ተለያዩ
Jan 16, 2026 76
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ነገሌ አርሲ እና ወላይታ ድቻ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ገ/መስቀል ዱባለ በ83ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ ነገሌ አርሲ መሪ ሆኗል። ሸገር ከተማ እና ፋሲል ከነማ ነጥብ ተጋሩ በፕሪሚየር ሊጉ ነጌሌ አርሲ ከወላይታ ድቻ ሸገር ከተማ ከፋሲል ከነማ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ ካርሎስ ዳምጠው በ94ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠረው ግብ ለወላይታ ድቻ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። ውጤቱን ተከትሎም አዲስ አዳጊው ነገሌ አርሲ በ26 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነትም ወደ አንድ ዝቅ የማድረግ ዕድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል። በሊጉ አምስተኛ ተከታታይ ድሉን የማስመዝገብ ሙከራውም አልተሳካም። ወላይታ ድቻ በ13 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኝ ሲሆን፤ ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም።
ሸገር ከተማ እና ፋሲል ከነማ ነጥብ ተጋሩ
Jan 16, 2026 80
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሸገር ከተማ እና ፋሲል ከነማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የፋሲል ከነማው የአማካይ ተጫዋች አቤኔዘር ዮሐንስ በ72ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ውጤቱን ተከትሎ ሸገር ከተማ በ15 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ፋሲል ከነማ በ26 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነትም ወደ አንድ ዝቅ የማድረግ እድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል።