ቀጥታ፡
ስፖርት
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከወራጅ ቀጠና የወጣበት ወሳኝ ድል አሳክቷል
Mar 9, 2026 35
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30/2018 (ኢዜአ)፦‎ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። መሐመድ ኑር ናስር ለድሬዳዋ ከተማ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከሁለት ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ27 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ወደ 13ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። በሊጉ ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ28 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ኢትዮጵያ መድን እና ሀድያ ሆሳዕና አንድ አቻ ተለያይተዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ታሪኩ ፀደቀ በ11ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ጎል ሀድያ ሆሳዕና መሪ መሆን ችሏል። አማኑኤል ኤርቦ በ30ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ግብ ለኢትዮጵያ መድን አንድ ነጥብ አስገኝታለች። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ25 ነጥብ ከነበረበት 17ኛ ደረጃ ወደ 16ኛ ከፍ በማለት ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። ሀድያ ሆሳዕና በ29 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ23ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ምድረ ገነት ሽሬ እና ፋሲል ከነማ አንድ አቻ ሲለያዩ ባህርዳር ከተማ እና ነገሌ አርሲ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ አቻ ተጠናቋል።
ፋሲል ከነማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ነጥብ ተጋሩ
Mar 9, 2026 53
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30/2018 (ኢዜአ)፦‎ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች መካሄዳቸውን ቀጥለዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ፋሲል ከነማ እና ምድረ ገነት ሽሬ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በረከት ግዛው በ56ኛው ደቂቃ ፋሲል ከነማን መሪ ያደረገችው ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ዳንኤል ዳርጌ በ89ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል ለምድረ ገነት ሽሬ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። ፋሲል ከነማ በ34 ነጥብ ደረጃውን ከሰባተኛ ወደ ስድስተኛ ከፍ አድርጓል። ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ምድረ ገነት ሽሬ በ27 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም።   በሌላኛው መርሐ-ግብር ባህርዳር ከተማ እና ነገሌ አርሲ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ባህርዳር ከተማ በ28 ነጥብ ደረጃውን ከ12ኛ ወደ 9ኛ ከፍ አድርጓል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ነገሌ አርሲ በ38 ነጥብ ከነበረበት ሶስተኛ ደረጃ ወደ ሁለተኛ ከፍ ብሏል። ነገሌ አርሲ ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ የማድረግ እድል አልተጠቀመበትም። ኢትዮጵያ መድን ከሀድያ ሆሳዕና በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም፣ ድሬዳዋ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተመሳሳይ ከምሽቱ 12 ላይ ይጫወታሉ።
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን ለማስተናገድ መመረጧ የስኬታማ የልማት ጉዞ ማሳያ ነው
Mar 9, 2026 82
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናን እንድታስተናግድ መመረጧ በሁሉም መስኮች እያስመዘገበች ለምትገኘው የልማት ሥራዎች ውጤት ማሳያ መሆኑን ታዋቂ አትሌቶች ገለጹ። ‎ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በመጪው ሚያዚያ ወር የሚካሄድ ዓለም አቀፍ ውድድርን እንድታዘጋጅ በዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ተመርጣለች፡፡ በውድድሩ ከተለያዩ ሀገራት የተውጣጡ አትሌቶች የሚሳተፉበት ከመሆኑ ባሻገር በውድድሩ አሸናፊ የሚሆኑ አትሌቶች ከፍተኛ ሽልማት የሚያገኙበት ይሆናል።   የኢትዮጵያን መመረጥ ተከትሎ ኢዜአ ያነጋገራቸው ታዋቂ አትሌቶች እንደገለጹት፤ ይህ አጋጣሚ ለኢትዮጵያ አትሌቲክስ ዕድገት አዲስ ምዕራፍ መክፈቱንና ሀገሪቱን በዓለም አቀፍ መድረክ የበለጠ ለማስተዋወቅ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል። ‎የአጭር ርቀት አትሌቷ ፋንቱ ሚጌሶ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ውድድርን እንድታዘጋጅ መመረጧ በርካታ ጠቀሜታዎች እንዳሉት ተናግራለች፡፡ ‎ለዚህ ስኬት ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የልማት ስራዎች፣ በተለይም የስታዲየሞች፣ የመሮጫ ትራኮችና የከተማው መሰረተ ልማት ግንባታ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ጠቁማለች። ‎ቀደም ሲል በሌሎች ሀገራት ስንሮጥ የምናየው ምቹ ሁኔታ፣ ዛሬ በሀገራችን እየተፈጠረ መሆኑን ገልጻ፤ ባለፉት ዓመታት በከተማ የታየው ለውጥ አስደናቂ መሆኑን ገልጻለች።   ‎ሌላዋ የረጅም ርቀት አትሌት መሰሉ መልካሙ፣ አዲስ አበባ ውድድሩን የማዘጋጀት ዕድል ማግኘት ለአትሌቲክሱ ከሚያበረክተው አስተዋጽኦ በተጨማሪ ሀገርን ለማስተዋወቅ ትልቅ እድል እንደሚፈጥር አስታውቃለች።‎ መንግሥት በተለያዩ አካባቢዎች እየገነባቸው ያሉ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች የስልጠና ማዕከላት የመሮጫ ትራኮች ለአትሌቶች ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን አንስታለች፡፡ ይህ ሁኔታ ለልምምድ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረ አንስታ በአትሌቲክሱ ለሚመዘገበው ውጤት የላቀ ድርሻ እንደሚኖረውም ጨምራ ተናግራለች።   የስልጠና ቦታዎችን ይበልጥ በማስፋፋት በረጅም ርቀት የምናስመዘግበውን ውጤት በአጭር ርቀት ለመድገም በትኩረት መሥራት እንደሚገባ አትሌቶቹ በአስተያየታቸው አመልክተዋል። ለዚህ ደግሞ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት እየተደረጉ ያሉ ስራዎችን ማጠናከር እንደሚገባም ነው የጠቆሙት።
በሊጉ ነገሌ አርሲ ከባህርዳር ከተማ ፋሲል ከነማ ከምድረገነት ሽሬ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ 
Mar 9, 2026 70
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30 /2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ባህርዳር ከተማ ከነገሌ አርሲ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ባህርዳር ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 22 ጨዋታዎች በአምስቱ አሸንፎ በአምስቱ ተሸንፎ በ12ቱ አቻ ወጥቷል። በ22ቱ ጨዋታዎች 15 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 17 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ27 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ነገሌ አርሲ በሊጉ 20 ጨዋታዎች አከናውኖ በ10ሩ ጊዜ ድል ሲቀናው በአምስቱ ተሸንፏል። ሰባት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። 22 ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎችን አስተናግዷል። አዲስ አዳጊው ነገሌ አርሲ በ37 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ባህርዳር ከተማ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ተሸንፏል። ተጋጣሚው ነገሌ አርሲ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ-ግብር ምድረ ገነት ሽሬ ከፋሲል ከነማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ምድረ ገነት ሽሬ እስከ አሁን በሊጉ ያሸነፈው የጨዋታ ብዛት ስድስት ነው። ስምንት ጊዜ ሲሸነፍ በተመሳሳይ ስምንት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 15 ግቦችን ሲያስቆጥር 16 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ26 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ በበኩሉ 22 ጨዋታዎችን አድርጎ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ አምስት ጊዜ ተሸንፏል። በስምንት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 16 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 14 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ፋሲል ከነማ በ33 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ምድረ ገነት ሽሬ በ22ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር በወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የ1 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ፋሲል ከነማ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ መድን ከሀዲያ ሆሳዕና በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ24 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሀዲያ ሆሳዕና በ28 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። በ22ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ መድን ከሸገር ከተማ፣ ሀዲያ ሆሳዕና ከአዳማ ከተማ በተመሳሳይ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታሉ። ድሬዳዋ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። ድሬዳዋ ከተማ በ28 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ24 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ድሬዳዋ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሁለት ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
የኤፍኤ ካፕ የጥሎ ማለፍ መርሐ-ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል
Mar 9, 2026 97
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 30/2018 (ኢዜአ)፡- የእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ ጥሎ ማለፍ (አምስተኛ ዙር) የመጨረሻ ጨዋታ ዛሬ በዌስትሃም ዩናይትድ እና ብሬንትፎርድ መካከል ይደረጋል። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ በለንደን ስታዲየም ይካሄዳል። ዌስትሃም ዩናይትድ በአራተኛው ዙር ማክስፊልድን፣ ብሬንትፎርድ በርተን አልቢዮንን በማሸነፍ ጥሎ ማለፍ ገብተዋል። ሁለቱ ክለቦች በኤፍ ካፕ ሲገናኙ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው።   ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ሶስት ጨዋታዎች ቡድኖቹ በተመሳሳይ አንድ ጊዜ ሲያሸንፉ በቀሪው ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። እ.አ.አ በ2023 ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ በነበራቸው ግንኙነት ዌስትሃም ዩናይትድ 1 ለ 0 በማሸነፍ ለአራተኛ ዙር አልፏል። ዌስትሃም ዩናይትድ ሶስት ጊዜ የኤፍኤ ካፕን ዋንጫ አንስቷል። ለመጨረሻ ጊዜ ውድድሩን ያሸነፈው እ.አ.አ በ1980 ነበር። የብሬንትፎርድ ትልቁ የኤፍኤ ካፕ ውጤት በአራት አጋጣሚዎች ለሩብ ፍጻሜ ያለፈባቸው ናቸው። የዛሬውን ጨዋታ የሚያሸንፈው ቡድን ሩብ ፍጻሜውን የሚቀላቀል የመጨረሻው ቡድን ይሆናል። የ42 ዓመቱ አንድሪው ማድሌይ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። አርሰናል፣ ማንችስተር ሲቲ፣ ቼልሲ፣ ሊቨርፑል፣ ሊድስ ዩናይትድ፣ ሳውዝሃምፕተን እና ፖርት ቫሌ ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀሉ ክለቦች ናቸው።
ሊድስ ዩናይትድ ሳውዝሃምፕተን እና ፖርት ቫሌ ለኤፍኤ ካፕ ሩብ ፍጻሜ አለፉ
Mar 8, 2026 124
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2018 (ኢዜአ)፦‎ በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ የጥሎ ማለፍ መርሐ-ግብር ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ተደርገዋል። ማምሻውን በኢላንድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሊድስ ዩናይትድ ኖርዊች ሲቲን 3 ለ 0 አሸንፏል። ሲን ሎንግስታፍ፣ ጋብርኤል ጉድሙንሰን እና ጆኤል ፒሮ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል።   በሌላኛው መርሐ-ግብር ሳውዝሃምፕተን ፉልሃምን 1 ለ 0 አሸንፏል። ሮስ ስቲዋርት በ90ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ግቧን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በእንግሊዝ ሶስተኛ የሊግ እርከን (ሊግ ዋን) የሚገኘው ፖርት ቫሌ ባልተጠበቀ ሁኔታ ሰንደርላንድን 1 ለ 0 ረቷል።   በቫሌ ፓርክ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቤን ዋይን በ28ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቶቹን ተከትሎ ሊድስ ዩናይትድ፣ ሳውዝሃምፕተን እና ፖርት ቫሌ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅለዋል። አጠቃላይ ሩብ ፍጻሜ የገቡ ክለቦች ብዛት ሰባት ደርሷል። አርሰናል፣ ማንችስተር ሲቲ፣ ቼልሲ እና ሊቨርፑል ሌሎች ሩብ ፍጻሜ የገቡ ክለቦች ናቸው። የእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ነገ በዌስትሃም ዩናይትድ እና ብሬንትፎርድ መካከል ይደረጋል።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና በወላይታ ድቻ ተሸነፈ
Mar 8, 2026 73
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ተደርገዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ወላይታ ድቻ ሲዳማ ቡናን 3 ለ 1 አሸንፏል። ኪዳኔ አሰፋ፣ መልካሙ ቦጋለ እና ያሬድ ዳርዛ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አዲሱ ፈራሚ አቤል ያለው የሲዳማ ቡናን ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና በ42 ነጥብ ላይ ረግቷል። በውድድሩ ዓመቱ አምስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ወላይታ ድቻ በ26 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ደረጃ ወደ 13ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል።   በሌላኛው መርሐ-ግብር መቻል እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው የተደረገው በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ነው። ውጤቱን ተከትሎ መቻል በ35 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ሲይዝ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ25 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።   ሸገር ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን 1 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቢኒያም ፍቅሩ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ሸገር ከተማ በ27 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በ25 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ቡናን 2 ለ 1 ረቷል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ናትናኤል ዱባለ እና ሩዋንዳዊው ፓትሪክ ሲቦማና የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሀምዛ ሱልጣን ለኢትዮጵያ ቡና ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል።   ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ34 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ በ29 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
246ኛው የሚላን ደርቢ
Mar 8, 2026 75
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2018 (ኢዜአ) ፦ በጣልያን ሴሪአ የ28ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ኤሲ ሚላን እና ኢንተር ሚላን የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል።   ጨዋታው በሳንሲሮ ስታዲየም ምሽት 4 ሰዓት ከ45 ላይ ይካሄዳል። ኤሲ ሚላን በውድድር ዓመቱ 27 ጨዋታዎችን አከናውኖ በ16ቱ ድል ሲቀናው ሁለት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ዘጠኝ ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 43 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 20 ግቦች ተቆጥረውበታል። ሚላን በ57 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የከተማ ተቀናቃኙ ኢንተር ሚላን በሊጉ ካደረጋቸው 27 ጨዋታዎች መካከል 22 ጊዜ ሲያሸንፍ አራት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 64 ግቦችን ሲያስቆጥር 21 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ67 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች በሁሉም ውድድሮች ሲገናኙ የአሁኑ ለ246ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 245 ጨዋታዎች ኢንተር ሚላን 91 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ኤሲ ሚላን 83 ጊዜ ሲያሸንፍ በቀሪዎቹ 71 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በሴሪአው 183 ጊዜ ተገናኝተው ኢንተር ሚላን 70፣ ኤሲ ሚላን 56 ጊዜ አሸንፈዋል። 57 ጊዜ ነጥብ ተጋርተዋል። ባለፉት 10 የሴሪአ ግንኙነታቸው ሁለቱም በተመሳሳይ አራት ጊዜ አሸንፈዋል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ጨዋታ ኤሲ ሚላን በክርስቲያን ፑሊሲች ጎል 1 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ክለቦቹ ለ117 ዓመታት የዘለቀ ተቀናቃኝነት አላቸው። ኢንተር ሚላን 20 እና ኤሲ ሚላን 19 ጊዜ የሴሪአ ዋንጫን አንስተዋል። በአህጉራዊ መድረክም ኤሲ ሚላን የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግን ሰባት ጊዜ በማንሳት ስኬታማው ክለብ ነው። ኢንተር ሚላን ሶስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሆኗል። በውድድር ዓመቱ ጠንካራ ፉክክር እያደረጉ የሚገኙት ክለቦች የሴሪአ ጨዋታ የተመልካቾችን ቀልብ ስቧል። ኢንተር ሚላን ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። በአንጻሩ ኤሲ ሚላን ድል ከቀናው በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያገኛል። የ48 ዓመቱ ዳንኤሌ ዴቬሪ ተጠባቂውን የደርቢ ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
የኤፍኤ ካፕ ጥሎ ማለፍ የሶስተኛ ቀን ውሎ
Mar 8, 2026 70
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 29/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ አምስተኛ ዙር መርሐ-ግብር የሶስተኛ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ።   ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ፉልሃም ከሳውዝሃምፕተን በክራቨን ኮቴጅ ስታዲየም ይጫወታሉ። በአራተኛው ዙር ፉልሃም ስቶክ ሲቲን፣ ሳውዝሃምፕተን ሌይስተር ሲቲን አሸንፈዋል። ፉልሃም በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ፣ ሳውዝሃምፕተን በሻምፒዮንሺፕ (ሁለተኛ ዲቪዚዮን) የሚገኙ ክለቦች ናቸው።   በሌላኛው መርሐ-ግብር ፖርት ቫሌ ከሰንደርላንድ ከቀኑ 10 ከሰዓት ከ30 ላይ በቫሌ ፓርክ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በእንግሊዝ ሶስተኛ የሊግ እርከን (ሊግ ዋን) የሚገኘው ፖርት ቫሌ በአራተኛው ዙር ብሪስቶል ሲቲን በማሸነፍ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅሏል። የፕሪሚየር ሊጉ ክለብ ሰንደርላንድ ኦክስፎርድ ዩናይትድን በመርታት 16 ውስጥ ገብቷል።   ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ሊድስ ዩናይትድ ከኖርዊች ሲቲ ይጫወታሉ። በአራተኛው ዙር ሊድስ ዩናይትድ በርሚንግሃም ሲቲን፣ ኖርዊች ሲቲ ዌስትብሮሚች አልቢዮንን በማሸነፍ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅለዋል። አሸናፊ ቡድኖች ለሩብ ፍጻሜ ያልፋሉ። ሊቨርፑል፣ አርሰናል፣ ቼልሲ እና ማንችስተር ሲቲ እስከ አሁን ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀሉ ክለቦች ናቸው።
በሴቶች ድምፅና ተሳትፎ የኢትዮጵያ ብልፅግና እውን ይሆናል- ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Mar 8, 2026 116
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2018(ኢዜአ)፦ በሴቶች ድምፅና ተሳትፎ የኢትዮጵያን ብልፅግና እናረጋግጣለን ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። 50ኛው ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀንን ምክንያት በማድረግ የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር በአዲስ አበባ ተካሄዷል። ስፖርታዊ መርሃ ግብሩ ‎የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ከሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ጋር በመተባበር የተዘጋጀ ነው። ‎‎የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በወቅቱ ባስተላለፉት መልዕክት፣ ሴቶች በሀገር ግንባታና በብልፅግና ጉዞ ውስጥ ያላቸውን የማይተካ ሚና አጽንኦት ሰጥተዋል። ‎በኢትዮጵያ ታሪክ በርካታ ስኬተማ ሰዎችና ዝነኛ አትሌት ሴቶች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ ይህ የላቀ ብቃትና ጥንካሬ ትልቅ እውቅና ሊሰጠው እንደሚገባ ገልጸዋል። ‎ሴቶች ለኢትዮጵያ ሰላምና ብልፅግና ትልቅ መስዋዕትነት መክፈላቸውን ያስታወሱት ከንቲባዋ፤ አሁንም ሴቶች ሀገራዊ ዕድገትን ለማረጋገጥ ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። ‎ከወንድሞቻችን ጋር ተሳስረን ሀገራችንን እናሳድጋለን በማለት የሴቶች ተሳትፎ ከወንዶች ጋር በተቀናጀና በተደጋገፈ መልኩ ለሀገር ግንባታ እንደሚውል አመልክተዋል። ‎ከንቲባዋ መንግሥት የሴቶችን ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ መሆኑንም አስታውቀዋል። ‎በብልፅግና ጉዞ ውስጥ የሴቶች የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ተጠቃሚነት በፍትሐዊነት እውን እንዲሆን በትጋት እንደሚሰራም ቃል ገብተዋል። ‎ሴቶች የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ መሪ ኃይል መሆናቸውን የገለጹት ከንቲባዋ፤ ቀኑን ምክንያት በማድረግ እንኳን አደረሳችሁ ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል። ‎የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ‎ላለፉት 50 ዓመታት የሴቶች መብትና ድምፅ ትኩረት እንዲያገኝ በተደረገው ጥረት፣ ዛሬ ላይ ለደረሰው ትልቅ ሀገራዊ ለውጥ መሠረት መጣሉን ገልጸዋል። ‎ሴቶች በፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ዘርፎች እያመጡት ያለው ውጤት ለሀገሪቱ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን አውስተዋል። ‎የሴቶች መብት እንዲከበርና የውሳኔ ሰጪነት ሚናቸው እንዲያድግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በመጠቆም፣ እንኳን አደረሳችሁ ሲሉ መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል። በውድድሩ የተሳተፉ ሴቶች ሩጫው የሴቶችን የአካልና የአዕምሮ ጤና ከመጠበቅ ባለፈ፣ ማህበራዊ ግንኙነትን በማጠናከር ረገድ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። ‎በ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ሀላፊዎች ተዋቂ አትሌቶችን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 17ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
Mar 8, 2026 55
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 17ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ-ግብር በሲዳማ ቡና እና መቻል መካከል ዛሬ ይደረጋል። ጨዋታው ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳል። ሲዳማ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው 16 ጨዋታዎች በስድስቱ ድል ሲቀናው በሰባቱ ተሸንፏል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 16 ግቦችን ሲያስቆጥር 22 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ21 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በበኩሉ በ16 ጨዋታዎች በዘጠኙ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 26 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 10 ጎሎች ተቆጥረውበታል። መቻል በ32 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ16ኛ ሳምንት ሲዳማ ቡና አዳማ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። መቻል ከሸገር ከተማ ሁለት አቻ ተለያይቷል። ሲዳማ ቡና ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ፣ መቻል ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያው ዙር በአራተኛ ሳምንት ባደረጉት ጨዋታ ሁለት አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በወቅቱ ቱሪስት ለማ ሁለቱን ግቦች ለመቻል አስቆጥራለች። ምትኬ ብርሃኑ የሲዳማ ቡናን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፋለች።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከወላይታ ድቻ ጋር ይጫወታል
Mar 8, 2026 59
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዛሬ ይጀመራል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ወላይታ ድቻ ከሲዳማ ቡና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወላይታ ድቻ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 22 ጨዋታዎች በአራቱ አሸንፎ በሰባቱ ተሸንፎ 11 ጊዜ አቻ ወጥቷል። 23 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያሳርፍ 25 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ23 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና 22 ጨዋታዎችን አከናውኖ 11 ጊዜ ሲያሸንፍ በሁለቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ዘጠኝ ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 27 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 11 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሲዳማ ቡና በ42 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ጨዋታው ወላይታ ድቻ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ሲዳማ ቡና ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። ሲዳማ ቡና ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። በሌላኛው መርሐ-ግብር መቻል ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቻል በውድድር ዓመቱ 22 ጨዋታዎችን አድርጎ ዘጠኙን ሲያሸንፍ በስድስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። ሰባት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 15 ግቦችን በ22ቱ ጨዋታዎች ላይ 29 ግቦችን ሲያስቆጥር 19 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ34 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በሊጉ ካከናወናቸው 22 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ያሸነፈው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በበኩሉ ስምንት ጊዜ ተሸንፏል። ዘጠኝ ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 16 ግቦችን ሲያገባ 23 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ24 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። መቻል እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በድል ጉዟቸው ለመቀጠል ይፋለማሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከኢትዮጵያ ቡና ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ31 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ቡና አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ29 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች በአሸናፊነት መንገድ ለመቀጠል የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ የሚደረገው ጨዋታ ሸገር ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስን ያገናኛል። ሸገር ከተማ በ24 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ25 ነጥብ 13ኛ ላይ ተቀምጧል። ሸገር ከተማ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ በበኩሉ ባለፉት ሰባት ጨዋታዎች ድል አልቀናቸውም። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታሉ። የ23ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር እስከ መጋቢት 1 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ አዲስ ግደይ እና የፋሲል ከነማው ታምራት ኢያሱ በተመሳሳይ ስምንት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በጋራ እየመሩ ነው።
ቼልሲ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል
Mar 8, 2026 66
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2018 (ኢዜአ)፦‎ በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ ጥሎ መርሐ-ግብር ቼልሲ ሬክሳምን 4 ለ 2 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በሬስኮርስ ግራውንድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆሽ አቼምፖንግ፣ አሌሃንድሮ ጋርናቾ፣ ጆአኦ ፔድሮ እና የሬክሳም ግብ ጠባቂ አርቱር ኦኮንኮ በራሱ ላይ ለሰማያዊዎቹ ግቦቹን አስቆጥረዋል።   ሳም ስሚዝ እና ካሉም ዶይል ለሬክሳም ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።   ጨዋታው በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሁለት አቻ በመጠናቀቁ ወደ ጭማሪ ሰዓት አምርቷል። አሌሃንድሮ ጋርናቾ በ96ኛው እና ጆአኦ ፔድሮ በ125ኛው ደቂቃ ያስቆጠሯቸው ጎሎች ቼልሲን ባለድል አድርጓል። ሉዊስ ብሩንት በ114ኛው ደቂቃ ለሬክሳም ያስቆጠረው ጎል በቪዲዮ የታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ከጨዋታ ውጪ በመሆኑ ተሽሯል። የሬክሳሙ ጆርጅ ዶብሰን በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ማብቂያ ላይ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ይህም ቡድኑን ጭማሪ 30 ደቂቃውን በ10 ተጫዋች እንዲጨርስ አስገድዶታል።   ጨዋታው አዝናኝ እንቅስቃሴ ተደርጎበታል። የስምንት ጊዜ የኤፍኤ ካፕ አሸናፊው ቼልሲ ለሩብ ፍጻሜ አልፏል። በእንግሊዝ ሁለተኛ ዲቪዚዮን (ሻምፒዮንሺፕ) የሚጫወተው የዌልሱ ሬክሳም የኤፍኤ ካፕ ጉዞው አምስተኛ ዙር ላይ ተገቷል።
በክልሉ ያለውን ዕምቅ የባህል ስፖርት ሀብት ለማልማትና ለማስተዋወቅ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው
Mar 7, 2026 75
ባሕር ዳር፤ የካቲት 28/2018 (ኢዜአ)፦በክልሉ ያለውን ዕምቅ የባህል ስፖርት ሀብት ለማልማትና ለማስተዋወቅ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን የአማራ ክልል ባህልና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ መልካሙ ፀጋዬ ገለጹ፡፡ በባሕር ዳር ከተማ አስተናጋጅነት በድምቀት ሲካሄድ የሰነበተው 23ኛው የአማራ ክልል የባህል ስፖርቶች ውድድር በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን አጠቃላይ አሸናፊነት ተጠናቅቋል። ረቂቅ አዋጁ የስፖርት እድገትን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል በባሕር ዳር ከተማ ለአንድ ሳምንት የተካሄደው ይህ ውድድር "ስፖርትና ጥበባት ለኢትዮጵያ ማንሰራራት" በሚል መሪ ቃል ነው የተከናወነው። ‎ በውድድሩ ማጠቃለያ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የክልሉ ባህልና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ መልካሙ ፀጋዬ እንደገለጹት፤ ክልሉ ያለውን ዕምቅ የባህል ስፖርት ሀብት ለማልማትና ለማስተዋወቅ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ይገኛል። ‎   ከየካቲት 22/2018 ዓ.ም ጀምሮ በትግል፣ በገበጣ፣ በቡብ፣ በሻህ፣ በቀስት ውርወራ፣ በገና ጨዋታ፣ በኮርቦና በሌሎች ዘርፎች ሲካሄድ የሰነበተው የባህል ስፖርት ውድድር፣ የእርስ በርስ ትስስርን በማጠናከር ውጤታማ በሆነ መልኩ መጠናቀቁን ገልፀዋል። ‎ በተለይም የክልሉን የባህል ስፖርት እሴቶች ሳይበረዙና ሳይከለሱ ከትውልድ ወደ ትውልድ ለማስተላለፍ የተጀመረው ተግባር በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስገንዝበዋል። ‎ በየዘርፉ በተካሄዱ የባህል ስፖርት ውድድሮች የተሻለ ውጤት ያስመዘገቡ አሸናፊዎች፣ በቀጣይ በሐረር ከተማ በሚካሄደው 17ኛው የባህልና ጥበባት ፌስቲቫል እና 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር ላይ ክልሉን ወክለው ለላቀ ውጤት እንዲዘጋጁም አሳስበዋል።   ‎የውድድሩ አጠቃላይ አሸናፊ የሆነው የአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ቃልአብ ከሃሊ በበኩላቸው፤ ዞኑ የአጠቃላይ ዋንጫ ሻምፒዮን በመሆን ሲሸለም የዘንድሮው ለ5ኛ ጊዜ መሆኑን ገልፀዋል። ‎ ዞኑ በአጠቃላይ አሸናፊ ሊሆን የቻለው በቀስት ውርወራ እና ገበጣን ጨምሮ በ8 የባህል ስፖርት ውድድሮች መሆኑን አስረድተዋል። ‎   በሴቶች ገበጣ 12 ጉድጓድ ውድድር 1ኛ በመሆን የሜዳልያና የዋንጫ ተሸላሚ የሆነችው ደግሞ የደቡብ ጎንደር ዞን ተወዳዳሪ ወጣት አይናዲስ አየነው ናት። በሀገር አቀፍ ደረጃ በሚካሄደው ውድድር ክልሏን ወክላ በመሳተፍ አሸናፊ ለመሆን ከወዲሁ መዘጋጀቷንም ገልፃለች።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም