ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
አርሰናል በኤፍኤ ካፕ ወደ አምስተኛ ዙር አለፈ
Feb 15, 2026 47
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 8/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ የአራተኛ ዙር መርሐ-ግብር አርሰናል ዊጋን አትሌቲክን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኖኒ ማዱዌኬ፣ ጋብርኤል ማርቲኔሊ፣ ጋብርኤል ጄሱስ እና የዊጋን አትሌቲኩ ጃክ ሃንት በራሱ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ላይ አርሰናል ከፍተኛ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። ሁለት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን ያቀበለው ኤበረቺ ኤዘ የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ አርሰናል ወደ አምስተኛ ዙር አልፏል። አርሰናል የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን 14 ጊዜ በማንሳት ስኬታማው ክለብ ነው። በሊግ ዋን የሚገኘው የአንድ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ዊጋን አትሌቲክ የኤፍኤ ካፕ ጉዞው አራተኛ ዙር ላይ ተገቷል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ፉልሃም፣ ሊድስ ዩናይትድ፣ ሰንደርላንድ እና ዎልቭስ ተጋጣሚዎቻቸውን በማሸነፍ ወደ አምስተኛ ዙር አልፈዋል።
ማንችስተር ሲቲ በኤፍኤ ካፕ ወደ አምስተኛ ዙር አለፈ
Feb 14, 2026 79
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 7/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ የአራተኛ ዙር መርሐ-ግብር ማንችስተር ሲቲ ሳልፎርድ ሲቲን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማርክ ጌሂ እና የሳልፎርድ ሲቲው አልፊ ዶሪንግተን በራሱ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አዲስ ፈራሚው ማርክ ጌሂ በሲቲ ማልያ የመጀመሪያ ጎሉን አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ ወደ አምስተኛ ዙር አልፏል። በሊግ ቱ(አራተኛ ዲቪዚዮን) የሚገኘው ሳልፎርድ ሲቲ የኤፍኤ ካፕ ጉዞው አራተኛ ዙር ላይ ተገቷል።
የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ 65ኛ ዓመት የምስረታ በዓልን ምክንያት በማድረግ በሃዋሳ ከተማ የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር እየተካሄደ ነው
Feb 14, 2026 94
ሀዋሳ ፤ የካቲት 7/2018 (ኢዜአ)፡-በሀገር መከላከያ ሠራዊት የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ 65ኛ ዓመት የምስረታ በዓልን ምክንያት በማድረግ የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር በሀዋሳ ከተማ እየተካሔደ ነው። በውድድሩ ከተለያዩ ክለቦች የተውጣጡ ከ302 በላይ ታዋቂ ወንድና ሴት አትሌቶች ተሳትፈዋል። እንዲሁም ከመከላከያ ሠራዊት አባላት፣ ከሀዋሳ ከተማ ነዋሪዎችና ከአጎራባች ክልል ከተሞች ጭምር የተውጣጡና በጠቅላላ ቁጥራቸው ወደ 10 ሺህ የሚሆኑ ነዋሪዎች በመሳተፍ ላይ ናቸው። በሥነ-ስርዓቱ ላይ የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ሹማ አብደታ፣ ሜጀር ጄኔራል እንዳልካቸው ወልደኪዳን፤ ከፍተኛ መኮንኖች፣ የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጥራቱ በየነና የአስተዳደሩ አመራሮች ተገኝተዋል።
የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ 65ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በተለያዩ ዝግጅቶች ያከብራል
Feb 13, 2026 88
ሀዋሳ ፤የካቲት 6/2018 (ኢዜአ)፡-በሀገር መከላከያ ሠራዊት የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ 65ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን ከነገ የካቲት 7 እስከ 15 ድረስ በተለያዩ ዝግጅቶች ያከብራል። የዕዙን የምስረታ በዓል አከባበር በማስመልከት ዛሬ መግለጫ የተሰጠ ሲሆን በዓሉ በነገው እለት በሀዋሳ ከተማ የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር በማካሄድ መከበር እንደሚጀምር ተመላክቷል። ከተመሰረተ 65 ዓመታት ዕድሜ ያስቆጠረው የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ ከፍተኛ ጀግንነትን የፈጸሙ ኮማንዶ፣ አየር ወለድና ልዩ የጸረ ሽብር ሀይሎችን ሲያሰለጥን ቆይቷል። እነዚህን የሀገር ባለውለታዎች ያፈራው የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ የመስረታ በዓሉን ምክንያት በማድረግ ነገ በሀዋሳ ከተማ ከማለዳው 12:00 ሰዓት ጀምሮ በወንዶችና በሴቶች ታዋቂ አትሌቶችን ጨምሮ ከሀዋሳና ከአጎራባች ከተሞች የተውጣጡ ከ10 ሺህ በላይ ሰዎች የሚሳተፉበት የሩጫ ውድድር እንደሚካሄድ ታውቋል። በሩጫ ውድድሩ ላይ ለመሳተፍም አትሌቶች ወደ ሀዋሳ ከተማ መግባታቸውን በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ኢንተርናሽናል ኮርስ ሜጀረር ተሾመ በቀለ ገልጸዋል። በዚህ ውድድር 202 ወንድና 80 ሴት ታዋቂ አትሌቶች እንደሚሳተፉ ገልጸው በአማራ፣ ኦሮሚያና ሲዳማ ክልሎች እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከሚገኙ ክለቦች እና በግል የሚወዳደሩ አትሌቶች ይሳተፋሉ ብለዋል። በውድድሩ በሁለቱም ጾታ ከአንደኛ እስከ አምስተኛ ለሚወጡ አትሌቶች እንደየደረጃቸው የገንዘብ ሽልማት እንደሚሰጥም አመልክተዋል። ውድድሩ መነሻና መድረሻውን ሀዋሳ ሱሙዳ አደባባይ ማድረጉንም ተጠቁሟል። የሲዳማ ክልል መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ሀላፊ አቶ ወሰንየለህ ስምኦን በበኩላቸው የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ 65ኛ ዓመት የምስረታ በዓል በድምቀት እንዲከበር ክልሉ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅቶች አድርጓል ብለዋል። መላው የሲዳማ ህዝብና የሀዋሳ ከተማ ነዋሪዎች የበዓሉ ታዳሚዎችን በእንግዳ ተቀባይነት ባህል ተቀብሎ ሊያስተናግድ እንደሚገባም አቶ ወሰንየለህ አሳስበዋል።
በስፔን ጥሎ ማለፍ የግማሽ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ አትሌቲኮ ማድሪድ ባርሴሎናን በሰፊ የግብ ልዩነት አሸነፈ
Feb 13, 2026 132
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፦ በስፔን ጥሎ ማለፍ (ኮፓ ዴል ሬይ) የግማሽ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ አትሌቲኮ ማድሪድ ባርሴሎናን 4 ለ 0 ረቷል። ማምሻውን በዋንዳ ሜትሮፖሊታኖ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አንቶዋን ግሪዝማን፣ ጁሊያን አልቫሬዝ፣ አዲስ ፈራሚው አዴሞላ ሉክማን እና የባርሴሎናው ግብ ጠባቂ ኤሪክ ጋርሺያ በራሱ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በመጀመሪያው አጋማሽ ፍጹም የጨዋታ ብልጫ የወሰደው አትሌቲኮ ማድሪድ በ45 ደቂቃ አራት ግቦችን አስቆጥሯል። የባርሴሎናው ተከላካይ ኤሪክ ጋርሺያ በ86ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ባርሴሎና በሁለተኛው አጋማሽ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ቢሞክርም አትሌቲኮ ማድሪድ ውጤቱን ማስጠበቅ ችሏል። አትሌቲኮ ማድሪድ ወደ ፍጻሜ የማለፍ እድሉን አስፍቷል። አስደንጋጭ ሽንፈት ያስተናገደው ባርሴሎና ውጤቱን የመቀልበስ ከባድ ፈተና በመልሱ ጨዋታ ይጠብቀዋል። የመልሱ ጨዋታ የካቲት 24 ቀን 2018 ዓ.ም በካምፕ ኑ ስታዲየም ይደረጋል። ትናንት በተደረገው ሌላኛው የስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ ሪያል ሶሳዬዳድ ከሜዳው ውጪ አትሌቲኮ ቢልባኦን 1 ለ 0 አሸንፏል። የመልሱ ጨዋታ የካቲት 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ባርሴሎና የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ነው።
አርሰናል ከብሬንትፎርድ ጋር አቻ ተለያየ
Feb 12, 2026 138
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ብሬንትፎርድ እና አርሰናል ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ አጠናቋል። ማምሻውን በጂቴክ ኮምዩኒቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኖኒ ማኑዌኬ በ61ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ በግንባሩ በመግጨት ያስቆጠረው ግብ መድፈኞቹን መሪ አድርጓል። በ71ኛው ደቂቃ ከረጅም እጅ ውርወራ የተገኘውን ኳስ ኪን ሉዊስ-ፖተር በግንባሩ ገጭቶ ከመረብ ላይ ባሳረፋት ጎል ብሬንትፎርድ አቻ ሆኗል። ብሬንትፎርድ በሊጉ ከእጅ ውርወራ አራተኛ ግቡን ማስቆጠር ችሏል። በጨዋታው አርሰናል ከብሬንትፎርድ ጠንካራ ፉክክር ገጥሞታል። ሁለተኛው አጋማሽ የተሻለ እንቅስቃሴ የተደረገበት ሲሆን ሁለቱም ቡድኖች ጨዋታውን የማሸነፍ እድላቸውን መጠቀም አልቻሉም። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ነጥብ የጣለው የሊጉ መሪ አርሰናል ነጥቡን ወደ 57 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ከስድስት ወደ አራት ዝቅ ብሏል። ብሬንትፎርድ በ40 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አልተሸነፈም።
ሊቨርፑል ሰንደርላንድን አሸነፈ
Feb 12, 2026 135
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 4/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት ጨዋታ ሊቨርፑል ሰንደርላንድን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በስታዲየም ኦፍ ላይት በተካሄደው ጨዋታ አምበሉ ቨርጅል ቫን ዳይክ በ61ኛው ደቂቃ ከማዕዘን ምት የተሻገረውን ኳስ በግንባሩ በመግጨት ያስቆጠራት ግብ ቀያዮቹን አሸናፊ አድርጋለች። በጨዋታው በመጀመሪያው አጋማሽ ሰንደርላንድ፣ ሊቨርፑል በሁለተኛው አጋማሽ ብልጫ ወስደው ተጫውተዋል። ጃፓናዊው የሊቨርፑል የተከላካይ አማካይ ዋታሩ ኤንዶ ባጋጠመው ከፍተኛ ጉዳት ምክንያት በ69ኛው ደቂቃ በጆ ጎሜዝ ተቀይሮ ወጥቷል። የሊቨርፑል የተከላካይ ክፍል ጉዳት ቀውስ ተባብሶ ቀጥሏል። በሊጉ 12ኛ ድሉን ያስመዘገበው የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ሊቨርፑል በ42 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሰንደርላንድ በ36 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት በሊጉ በሜዳው ሽንፈት ሳያስተናግድ የቆየው ብቸኛው ክለብ ሰንደርላንድ ለመጀመሪያ ጊዜ በስታዲየም ኦፍ ላይት ተሸንፏል። በሌላኛው ጨዋታ በርንሌይ ክሪስታል ፓላስን 3 ለ 2 አሸንፏል።
ማንችስተር ሲቲ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል
Feb 12, 2026 132
አዲስ አበባ፤ የካቲት 4/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ማንችስተር ሲቲ ፉልሃምን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶዋን ሴሜንዮ፣ ኒኮ ኦራይሊ እና አርሊንግ ሃላንድ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ማንችስተር ሲቲ በተጋጣሚው ላይ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። ውጤቱን ተከትሎ በውድድር ዓመቱ 16ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ በ53 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት በጊዜያዊነት ወደ ሶስት ዝቅ አድርጓል። ውሃ ሰማያዊዎቹ በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝተዋል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ፉልሃም በ34 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።በሊጉ ተከታታይ ሽንፈቱንም አስተናግዷል። የማንችስተር ሲቲው አጥቂ አርሊንግ ሃላንድ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ 22 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን አጠናክሯል። በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ-ግብር አስቶንቪላ ብራይተንን በታይሮን ሚንግስ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል። ውጤቱን ተከትሎ ቪላ ነጥቡን ወደ 50 ከፍ በማድረግ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ብራይተን በ31 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኖቲንግሃም ፎረስት እና ዎልቭስ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ማንችስተር ሲቲ ከፉልሃም ጋር ጨዋታውን ያከናውናል
Feb 11, 2026 155
አዲስ አበባ፤ የካቲት 4 /2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር የሁለተኛ ቀን ውሎ አምስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። በኢትሃድ ስታዲየም ማንችስተር ሲቲ ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ ፉልሃምን ያስተናግዳል። ማንችስተር ሲቲ በ50 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ፉልሃም በ34 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ25ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ማንችስተር ሲቲ ሊቨርፑልን 2 ለ 1 በማሸነፍ በዋንጫ ፉክክሩ የቆየበትን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ውሃ ሰማያዊዎቹ የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፉ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያላቸውን የነጥብ ልዩነት በጊዜያዊነት ወደ ሶስት ዝቅ ያደርጋሉ። ባለፉት ሁለት የሊጉ ጨዋታዎች ሽንፈት ያስተናገደው ፉልሃም ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ሰንደርላንድ ከሊቨርፑል ምሽት 5 ሰዓት ከ15 ላይ በስታዲየም ኦፍ ላይት ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሰንደርላንድ በ36 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ሊቨርፑል በ39 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱም ቡድኖች በ25ኛ ሳምንት ካስተናገዱት ሽንፈት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በሚያደርገው ፉክክር ከዛሬው ጨዋታ ሶስት ነጥብ ያስፈልገዋል። አስቶንቪላ ከብራይተን፣ ክሪስታል ፓላስ ከበርንሌይ እና ኖቲንግሃም ፎረስት ከዎልቭስ በተመሳሳይ ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ።
ቼልሲ ነጥብ ጥሏል
Feb 10, 2026 132
አዲስ አበባ፤ የካቲት 3/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ቼልሲ እና ሊድስ ዩናይትድ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆአኦ ፔድሮ በ24ኛው ደቂቃ እና ኮል ፓልመር በ58ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ባስቆጠሯቸው ግቦች ቼልሲ 2 ለ 0 መምራት ችሎ ነበር። ሉካስ ንሜቻ በ67ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት እና ኖህ ኦካፎር በ73ኛው ደቂቃ በጨዋታ የሊድስን የአቻነት ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ባለሜዳው ቼልሲ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ፉክክሩ ወሳኝ ነጥብ ጥሏል። በሌላኛው ጨዋታ ኒውካስትል ዩናይትድ በማሊክ ታው እና ጃኮብ ራምሴይ ግቦች ቶተንሃም ሆትስፐርስን 2 ለ 1 አሸንፏል። አርቺ ግሬይ ለቶተንሃም ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቦርንማውዝ ኤቨርተንን 2 ለ 1 አሸንፏል።
ማንችስተር ዩናይትድ ከዌስትሃም ዩናይትድ ጋር አቻ ተለያየ
Feb 10, 2026 119
አዲስ አበባ፤ የካቲት 3/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 26ኛ ሳምንት ጨዋታ ዌስትሃም ዩናይትድ እና ማንችስተር ዩናይትድ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። ማምሻውን በለንደን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቶማስ ሶቼክ በ50ኛው ደቂቃ የዌስትሃም ዩናይትድን የመሪነት ግብ አስቆጥሯል። ጨዋታው በዌስትሃም አሸናፊነት ተጠናቀቀ ሲባል ተቀይሮ የገባው ቤንጃሚን ሼስኮ በ96ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግሩም ግብ ዩናይትድን አቻ አድርጓል። ማንችስተር ዩናይትድ በጨዋታው ብልጫ ቢወስድም ግልጽ የግብ እድሎችን ለመፍጠር ተቸግሯል። ዌስትሃም ዩናይትድ በጥልቀት በመከላከል እና በመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴ ቢጫወትም ውጤቱን ማስጠበቅ አልቻለም። ከአራት ተከታታይ ድሎች በኋላ አቻ የወጣው ማንችስተር ዩናይትድ በ45 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ዩናይትድ ከሁለት ዓመታት በኋላ በሊጉ አምስት ተከታታይ ድል የማስመዝገብ ውጥን አልተሳካም። ዌስትሃም ዩናይትድ በ24 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ዌስትሃም ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ነጥብ ጥሏል።
የዓለም አትሌቲክስ የውድድር ዋና ዳይሬክተር ፒርስ ኦክላጋን የአትሌቲክስ መሰረተ ልማቶችን ጎበኙ
Feb 10, 2026 156
አዲስ አበባ፤ የካቲት 3/2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም አትሌቲክስ የውድድር ዋና ዳይሬክተር ፒርስ ኦክላጋን የአትሌቲክስ መሰረተ ልማቶችን ዛሬ ማለዳ ጎብኝተዋል። የውድድር ዋና ዳይሬክተሩ ፒርስ ኦክላጋን በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ግብዣ መሰረት ለጉብኝት ዛሬ አዲስ አበባ ገብተዋል። ዋና ዳይሬክተሩ በዓለም አትሌቲክስ እውቅና ያገኘው የአደይ አበባ ዓለም አቀፍ የመለማመጃ ትራክ እና የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚን ጎብኝተዋል። ፌዴሬሽኑ በቀጣይ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እና የአንድ ቀን ውድድሮች (One day meeting) ጨምሮ ሌሎች ዓለም አቀፍ እና አህጉር አቀፍ ውድድሮችን ለማዘጋጀት የሚያደርገው ዝግጅት የዳይሬክተሩ ጉብኝት ወሳኝ መሆኑ ተመላክቷል። በተጨማሪም የስፖርት ዲፕሎማሲ ግንኙነትን የማጠናከር ፋይዳ እንዳለውም የፌዴሬሽኑ መረጃ ያመለክታል። የዓለም አትሌቲክስ የውድድር ዋና ዳይሬክተር ፒርስ ኦክላጋን ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዲኤታ አቶ መኪዩ መሀመድ፣ ከፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት ኮማንደር አትሌት ስለሺ ስህን እና ከፌዴሬሽኑ የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባላት ጋር ውይይት አድርገዋል።
ማንችስተር ዩናይትድ ከዌስትሃም ዩናይትድ ጋር ጨዋታውን ያደርጋል
Feb 10, 2026 157
አዲስ አበባ፤ የካቲት 3/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዛሬ ይጀመራል። በዕለቱ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በለንደን ስታዲየም ዌስትሃም ዩናይትድ ከማንችስተር ዩናይትድ ጋር ምሽት 5 ሰዓት ከ15 ላይ ይጫወታሉ። ዌስትሃም ዩናይትድ በ23 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ማንችስተር ዩናይትድ በ44 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች መካከል ሶስቱን ያሸነፈው ዌስትሃም ዩናይትድ በጥሩ ወቅታዊ ብቃት ላይ ይገኛል። በጊዜያዊው አሰልጣኝ ማይክል ካሪክ የሚመራው ማንችስተር ዩናይትድ በሊጉ ያለፉትን አራት ተከታታይ ጨዋታዎች አሸንፏል። ዌስትሃም ዩናይትድ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት እያደረገ ባለው ብርቱ ፉክክር ሶስት ነጥብ እጅጉን ወሳኝ ነው። በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ እየተፎካከረ የሚገኘው ዩናይትድ በሊጉ አምስተኛ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ማንችስተር ዩናይትድ ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ አምስት ተከታታይ ጨዋታዎችን ያሸነፈው እ.አ.አ በ2023/24 የውድድር ዓመት ነው። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ43 ዓመቱ ሳይመን ሁፐር ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ቼልሲ ከሊድስ ዩናይትድ ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቼልሲ በ43 ነጥብ አምስተኛ፣ ሊድስ ዩናይትድ በ29 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዘዋል። ሁለቱም ቡድኖች በሊጉ ተከታታይ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይፋለማሉ። ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከኒውካስትል ዩናይትድ እና ኤቨርተን ከቦርንማውዝ በተመሳሳይ ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ።
በሊጉ ተስተካካይ መርሐ-ግብር ሀዲያ ሆሳዕና ፋሲል ከነማን አሸነፈ
Feb 9, 2026 114
አዲስ አበባ፤ የካቲት 2 /2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት ተስተካካይ ጨዋታ ሀዲያ ሆሳዕና ፋሲል ከነማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሱራፌል ተመስገን በ60ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ ስድስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ሀዲያ ሆሳዕና በ24 ነጥብ ደረጃውን ከ15ኛ ወደ 10ኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል። በአንጻሩ በሊጉ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ፋሲል ከነማ በ33 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ፋሲል ከነማ የሊጉ መሪ መሆን የሚችልበትን እድል መጠቀም አልቻለም። ሁለቱ ቡድኖች በ16ኛው ሳምንት ሊያደርጉት የነበረው ጨዋታ በጥምቀት በዓል ምክንያት ተራዝሞ በተስተካካይ መርሐ-ግብርነት መያዙ የሚታወስ ነው።
በተጠባቂው የደርቢ ጨዋታ ፒኤስጂ ማርሴይን አሸነፈ
Feb 9, 2026 143
አዲስ አበባ፤ የካቲት 2/2018 (ኢዜአ)፦ በፈረንሳይ ሊግ አንድ 21ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ-ግብር ፒኤስጂ ማርሴይን 5 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በፓርክ ደ ፕሪንስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኡስማን ደምበሌ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ክቪቻ ክቫርትሽኬሊያ፣ ካንግ ኢን-ሊ እና የማርሴዩ ፋኩንዶ መዲና በራሱ ላይ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ደምበሌ በፒኤስጂ ማልያ 50ኛ እና 51ኛ ግቦቹን አስቆጥሯል። በጨዋታው ፒኤስጂ ከፍተኛ ብልጫ ወስዷል። በውድድር ዓመቱ 16ኛ ድሉን ያስመዘገበው ፒኤስጂ በ51 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከሌንስ ተረክቧል። በአንጻሩ በሊጉ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ማርሴይ በ39 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። የ "Le Classique" ደርቢ በፒኤስጂ አሸናፊነት ተጠናቋል።
በሊጉ ተስተካካይ መርሐ-ግብር ፋሲል ከነማ ከሀዲያ ሆሳዕና ዛሬ ይጫወታሉ
Feb 9, 2026 134
አዲስ አበባ፤ የካቲት 2/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሐ-ግብር ፋሲል ከነማ ከሀዲያ ሆሳዕና ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታው ቀን 9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል። ፋሲል ከነማ በሊጉ ካደረጋቸው 18 ጨዋታዎች መካከል ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በዘጠኝ ጨዋታዎች ላይ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ 14 ግቦችን ሲያስቆጥር 7 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ33 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ፋሲል ከነማ በሊጉ ዝቅተኛ የግብ መጠን (7) የተቆጠረበት እና አነስተኛ ሽንፈት ያስተናገደ (1) ቡድን ነው። ተጋጣሚው ሀዲያ በውድድር ዓመቱ 18 ጨዋታዎችን አከናውኖ በአምስቱ ድል ሲቀናው ሰባት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ስድስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 16 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 20 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሀዲያ ሆሳዕና በ21 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ፋሲል ከነማ ካሸነፈ የመጀመሪያውን ዙር የሊጉ መሪ ሆኖ ያጠናቅቃል። ሶስት ነጥብ ሀዲያ ሆሳዕና ከወራጅ ቀጠና እንዲርቅ ያደርገዋል። ሁለቱ ቡድኖች በ16ኛው ሳምንት ሊያደርጉት የነበረው ጨዋታ በጥምቀት በዓል ምክንያት መራዘሙ የሚታወስ ነው።
በተጠባቂው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ሊቨርፑልን አሸነፈ
Feb 8, 2026 143
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ-ግብር ማንችስተር ሲቲ ከመመራት ተነስቶ ሊቨርፑልን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዶምኒክ ስቦዝላይ በ74ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ በቅጣት ምት ባስቆጠረው ግብ ቀያዮቹ መሪ ሆነዋል። በርናንዶ ሲልቫ በ84ኛው ደቂቃ በጨዋታ እና አርሊንግ ሃላንድ በ93ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት የማንችስተር ሲቲን የማሸነፊያ ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ላይ ለሊቨርፑል ግቧን ያስቆጠረው ዶምኒክ ስቦዝላይ በ103ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ሃላንድ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ 21 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን አጠናክሯል። በጨዋታው ማንችስተር ሲቲ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድል በመፍጠር የተሻለ ነበር። በሊጉ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ ነጥቡን ወደ 50 ከፍ በማድረግ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ ስድስት ዝቅ ብሏል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል በ39 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ክሪስታል ፓላስ በኢስማይላ ስር ግብ ብራይተንን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ25ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ተጠናቋል። የ26ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከየካቲት 3 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳሉ።
ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ትኩረት ተሰጥቷል-ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ
Feb 8, 2026 148
አዳማ፤ የካቲት 1/2018 (ኢዜአ)፦ስፖርትን ለስነ ምግባር ግንበታና ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ያለውን እቅም ለማሳካት ትኩረት መሰጠቱን የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ ገለፁ። ሀገር አቀፍ የታዳጊ ወጣቶች ስፖርት ስልጠና ምዘና ውድድር "የተተኪ ስፖርተኞች ልማት፤ ለስፖርታችን እድገት" በሚል መሪ ሐሳብ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ዛሬ ተጀምሯል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ በወቅቱ ስፖርትን ለስነ ምግባር ግንባታና ተተኪዎችን ለማፍራት ያለውን አቅም ለማሳካት ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። ስፖርትን ለሀገር ገፅታ ግንባታና የህዝብ ለህዝብ ትስስር ሚናን ለማጉላት እንዲቻል በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራትም የምልመላና ስልጠና ስርዓት ከመዘርጋት ጎን ለጎን ለስፖርት መሰረተ ልማት ተደራሽነት ትኩረት መሰጠቱን አንስተዋል። ባለፉት ስምንት ዓመታት 17 ሺህ 636 የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች በሀገሪቷ ተገንብተው ለታዳጊዎች የአካልና የአእምሮ ብቃት ማጎልበቻ አገልግሎት እንዲውሉ መደረጉን ገልጸዋል። ዛሬ በአዳማ የተጀመረው ውድድርም ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ወሳኝ ሚና እንዳለው ጠቁመዋል። የኦሮሚያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ሃላፊ ሮዛ ቢያ እንደተናገሩት፥ ክልሉ ለስፖርት ልማት ዘርፍ ትኩረት በመስጠት ስልጠናዎችን እየሰጠ ነው። የስፖርት ልማትን ለማሳካት የክልሉ ከተሞችና ወረዳዎች የስፖርት ማዘወተሪያዎችን ከኮሪደር ልማት ጋር በማቆራኘት እየሰሩ መሆኑን ጠቁመዋል። ዛሬም በ15 የስፖርት አይነቶች ከሁሉም ክልሎች የተወጣጡ ከ3ሺህ በላይ ታዳጊዎች በውድድር እየተሳተፉ ይገኛሉ ብለዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው ከተማዋን ለነዋሪው ምቹ ለማድረግ የስፖርትና ሌሎች መሰረተ ልማቶች እየተገነቡ ይገኛሉ ብለዋል። ታዳጊዎች በአእምሮና በአካል ብቁ እንዲሆኑ የመዝናኛና ስፖርት ስፍራዎች በከተማዋ በስፋት እየተገነቡ መሆኑን አስረድተዋል። የኢዜአ የዲጂታል ሚዲያ ገጾች ፦ https://linktr.ee/ENADigital
ፒኤስጂ እና ማርሴይ ዛሬ የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ ይጠበቃል
Feb 8, 2026 119
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2018(ኢዜአ):- በፈረንሳይ ሊግ አንድ 21ኛ ሳምንት ፒኤስጂ ከማርሴይ ይጫወታሉ። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ከ45 በፓርክ ደ ፕሪንስ ስታዲየም ይካሄዳል። ፒኤስጂ በ48 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ማርሴይ በ39 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የፓሪሱ ክለብ ፒኤስጂ በሊጉ 20 ጨዋታዎችን አድርጎ 15ቱን ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ20 ጨዋታዎች 43 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 16 ጎሎችን አስተናግዷል። ተጋጣሚው ማርሴይ በበኩሉ በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 20 ጨዋታዎች መካከል በ12ቱ ድል ሲቀናው አምስት ጊዜ ተሸንፏል። በቀስታ ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 46 ግቦችን ሲያስቆጥር 22 ተቆጥረውበታል። ማርሴይ በሊጉ ከፍተኛ የግብ መጠን ያስቆጠረ ቡድን ነው። ሁለቱ ክለቦች በፈረንሳይ ሊግ 1 ሲገናኙ የዛሬው ለ45ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 44 ጨዋታዎች ፒኤስጂ 26 ጊዜ ሲያሸንፍ ማርሴይ በ10ሩ ድል ቀንቶታል። ስምንት ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። ባለፉት አምስት የሊግ የእርስ በእርስ ጨዋታዎች ፒኤስጂ አራትት ጊዜ ሲያሸንፍ ማርሴይ አንድ ጊዜ ድል ቀንቶታል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ "Le Classique" የሚል ስያሜ አለው። የሁለቱ ቡድኖች ከእ.አ.አ 1970ዎቹ መጀመሪያ አንስቶ ታሪካዊ ተቀናቃኝነት አላቸው። ፒኤስጂ በፈረንሳይ መዲና ፓሪስ የሚገኝ እና የሀብታሞች ከተማ እየተባለ ይጠራል። የወደብ ከተማ የሆነችው ማርሴይ የሰራተኛ ማህረሰብ የሚኖርባት እና በከተማቸው ጉዳይ ወግ አጥባቂ የሚባሉ ዜጎች የሚኖሩባት ከተማ ናት። ይህ ከእግር ኳሱ ባለፈ የፖለቲካና የኢኮኖሚው ጉዳይ ተቀናቃኝነቱን የበለጠ አጋግሎታል። ፒኤስጂ የፈረንሳይ ሊግ አንድ 13 ጊዜ አሸንፏል። ባለፉት ዓመታት በሊጉ የበላይነቱን ይዟል። ክለቡ የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ነው። ተቀናቃኙ ማርሴይ ዘጠኝ ጊዜ ሊጉን ማሸነፍ ችሏል። የሊግ ውድድሩን ለመጨረሻ ጊዜ ያሸነፈው እ.አ.አ 1988/89 የውድድር ዓመት ነው። ሁለቱ ክለቦች የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግን ያነሱ የፈረንሳይ ክለቦች ናቸው። ፒኤስጂ የወቅቱ የውድድሩ የዋንጫ ባለቤት ነው። የዛሬው ጨዋታ ፒኤስጂ መሪነቱን ከሌንስ ለመረከብ፣ ማርሴይ በአውሮፓ መድረክ የመሳተፍ ህልሙን ለማስቀጠል የሚያደርጉት ነው። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት የሊግ ጨዋታ ማርሴይ በናይፍ አገርድ ግብ 1 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። የ33 ዓመቱ ዊሊ ዴላጆድ ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። የዘንድሮው የፈረንሳይ ሊግ 1 ክስተት የሆነው ሌንስ በ49 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው።
ልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክ 2018 የግማሽ ማራቶን የጎዳና ላይ ሩጫ በሀዋሳ ሀይቅ ዳርቻ ተካሄደ
Feb 8, 2026 141
ሀዋሳ ፤ የካቲት 1/2018(ኢዜአ):-ልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክ 2018 የግማሽ ማራቶን የጎዳና ላይ ሩጫ በሀዋሳ ሀይቅ ዳርቻ ተካሄደ። ከአንኮበር እስከ ሀረር በሚል የልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክ 2018 የሩጫ ውድድር በተለያዩ ከተሞች እየተካሄደ ይገኛል። በሀዋሳ ሃይቅ ዳርቻ ዛሬ በተካሄደው የግማሽ ማራቶን ውድድር የአዲስ አበባ ፖሊስ አትሌቶቹ ስማቸው ወልዴ ወንዶች እና ቤተልሄም አስማረ በሴቶች አሸናፊ ሆነዋል። በወንዶች በግል የተወዳደሩት አትሌት ጌታቸው ኪዳኔ እና ሱልጣን አብደላ በቅደም ተከተል 2ኛ እና 3ኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቀዋል። በሴቶች ትነበብ ነጋ ከአዲስአበባ ፖሊስ፤ ያተኔ ኮሞሼ ከኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን ይዘው ውድድሩን አጠናቀዋል። በግማሽ ማራቶን ከተደረገው የሁለቱም ጾታ አትሌቶች ውድድር በተጨማሪ በአንጋፋ አትሌቶች፣ እንዲሁም በታዳጊዎችና በህጻናት የአራት ኪሎሜትርና የአዋቂዎች የ8 ኪሎሜትር ውድድር ተከሂዷል። ከአትሌቶች አንደኛ ለወጡት የ100 ሺህ ብር፤ ለሁለተኛ 50ሺህ ብር፤ ሶስተኛ ለወጡት የ15 ሺህ ብር ሽልማት ተሰጥቷቸዋል። ከአንኮበር እስከ ሀረር በሚል እየተካሄደ ያለው የልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክ 2018 የሩጫ ውድድር በቀጣይ በጅማ፣ አርባምንጭ፣ በቆጂና ሀረር ከተሞች እንደሚካሄድ ተጠቁሟል። በኢትዮ ቴሌኮም ስያሜ የተካሄደው የሀዋሳ ሀይቅ ግማሽ ማራቶን ውድድር ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት መሆኑ ተገልጿል።