ስፖርት
የመጀመሪያው የፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ ዛሬ ይጀመራል
Jun 14, 2025 56
አዲስ አበባ ሰኔ 7/2015(ኢዜአ):- የመጀመሪያው የፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ በአሜሪካ አስተጋጅነት ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል። በምድብ አንድ የሚገኙት አል አህሊ ከኢንተር ሚያሚ ከሌሊቱ ዘጠኝ ሰዓት በሚያሚ ሀርድ ሮክ ስታዲየም የመክፈቻ ጨዋታውን ያደርጋሉ። እ.አ.አ በ2000 የተጀመረው ውድድር (ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ) ከዚህ ቀደም አህጉራዊ የክለቦች ውድድርን ያሸነፉ ክለቦች የሚሳተፉበት ነበር። ዓለም አቀፉ የፊፋ በአዲስ መልክ ባስተዋወቀው አሰራር መሰረት ነባሩን ፎርማት በመሻር የተሳታፊ ክለቦችን ቁጥር ወደ 32 አሳድጓል። በዚሁ መሰረት ቡድኖቹ በስምንት ምድብ ተከፍለው ለአራት ሳምንታት 63 ጨዋታዎች በ11 የአሜሪካ ከተሞች ያደርጋሉ። በምድብ አንድ አል አህሊ፣ ኢንተር ሚያሚ፣ ፓልሜራስ እና ፖርቶ፣ በምድብ 2 አትሌቲኮ ማድሪድ፣ ቦታፎጎ፣ ፒኤስጂ እና ሲያትል ሳውንደርስ፣ በምድብ 3 ኦክላንድ ሲቲ፣ ባየር ሙኒክ፣ ቤኔፊካ እና ቦካ ጁኒየርስ፣ በምድብ 4 ቼልሲ፣ ኤስፔራንስ፣ ፍላሚንጎ እና ሎስ አንጀለስ ኤፍሲ ይገኛሉ።   በምድብ አምስት ሪቨር ፕሌት፣ ኡርዋ ሬድ ዳይመንድስ፣ ሞንትሬይ እና ኢንተር ሚላን፣ ምድብ 6 ፍሉሜንሴ፣ ቦሩሲያ ዶርትሙንድ፣ ኡልሳን እና ማሜሎዲ ሳንዳውንስ፣ ምድብ 7 ማንችስተር ሲቲ፣ ዋይዳድ ካዛብላንካ፣ አል አይን እና ጁቬንቱስ፣ በመጨረሻው ምድብ 8 ሪያል ማድሪድ፣ አል ሂላል፣ ፓቹካ እና ሬድ ቡል ሳልበዝርግ ተደልድለዋል። በክለቦች የዓለም ዋንጫ ላይ ከአውሮፓ፣ ደቡብ አሜሪካ፣ ሰሜን አሜሪካ፣ አፍሪካ ፣ ማዕከላዊ አሜሪካ፣ ካሪቢያን እና ኦሺንያ ቀጣናዎች የሚገኙ ክለቦች ይሳተፋሉ። ፊፋ አህጉራት ባላቸው ወቅታዊ ብቃት እና ውጤት መሰረት ለአውሮፓ 12 (ዩኤፋ) ፣ ለደቡብ አሜሪካ (ኮንቤሞል) ስድስት፣ እስያ (4(፣ አፍሪካ (4) እና ሰሜን አሜሪካ ፣ ማዕከላዊ አሜሪካ እና ካሪቢያን (ኮንካካፍ) በተመሳሳይ አራት አግኝተዋል። አሜሪካ በአዘጋጅነቷ እና ኦሽንያ ባላት አህጉራዊ የክለብ ውጤት በተመሳሳይ አንድ አንድ የተሳትፎ ኮታ አግኝተዋል። ፊፋ ለውድድሩ ተሳታፊዎች የአንድ ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ሽልማት አዘጋጅቷል። የፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ እስከ ሐምሌ 6 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል።
የኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ 50ኛው የፕሪሚየር ሊግ የደርቢ ጨዋታ ይጠበቃል
Jun 14, 2025 54
አዲስ አበባ ሰኔ 7/2015(ኢዜአ):- የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ35ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ በሚያደርጉት ተጠባቂ ጨዋታ ዛሬ ይጀመራል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። በደረጃ ሰንጠረዡ ኢትዮጵያ ቡና በ55 ነጥብ 2ኛ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ45 ነጥብ 7ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። በአሰልጣኝ ነጻነት ክብሬ የሚመራው ኢትዮጵያ ቡና በፕሪሚየር ሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 32 ጨዋታዎች 16 ጊዜ ሲያሸንፍ 8 ጊዜ ተሸንፎ፤ 8 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በ32ቱ ጨዋታዎች 28 ግቦችን ሲያስቆጥር 16 ጎሎችን አስተናግዷል።   ተጋጣሚው ቅዱስ ጊዮርጊስ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው 32 ጨዋታዎች በ12ቱ አሸንፎ 11 ጊዜ ተሸንፏል። 9 ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። ኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ በፕሪሚየር ሊጉ እርስ በእርስ ሲገናኙ የዛሬው ለ50ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም 49 ጊዜ ተጫውተው ቅዱስ ጊዮርጊስ 21 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ሲይዝ ኢትዮጵያ ቡና 8 ጊዜ ድል ቀንቶታል። 20 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በ45ቱ ጨዋታዎች በድምሩ 95 ጎሎች የተቆጠሩ ሲሆን ፈረሰኞቹ 63 እንዲሁም ቡናማዎቹ ደግሞ 32 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ኢትዮጵያ ቡና የሊጉን ዋንጫ አንድ ጊዜ ያነሳ ሲሆን ቅዱስ ጊዮርጊስ 16 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። በሊጉ ኢትዮጵያ ቡና መልካም የሚባል ጊዜን ያሳለፈ ሲሆን በአንጻሩ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሚፈለገው የብቃት ደረጃ ላይ አልተገኘም። የሁለቱ ክለቦች በርካታ ደጋፊዎች ለጨዋታው ድምቀት ይሰጡታል ተብሎ ይጠበቃል። ቡድኖቹ በመጀመሪያው ዙር በሊጉ ባደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። ምሽት 12 ሰዓት ሻምፒዮንነቱን አስቀድሞ ያረጋገጠው ኢትዮጵያ መድን ከሀድያ ሆሳዕና ጋር ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ መድን በ67 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ሲቀመጥ ሀድያ ሆሳዕና በ47 ነጥብ 5ኛ ደረጃን ይዟል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ኮከብ ተጫዋች እጩዎች ይፋ ሆኑ
Jun 13, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበር የ2017 የሊጉን ኮከብ ተጫዋች እጩዎች ዝርዝር ዛሬ ይፋ አድርጓል። ተመልካቾች ለተጫዋቾች ድምጽ መስጠት የሚችሉበት አማራጭ ማዘጋጀቱንም ገልጿል። ማህበሩ ለኮከብ ተጫዋችነት እጩ የሆኑ ሰባት ተጫዋቾችን አሳውቋል። ከሻምፒዮኑ ኢትዮጵያ መድን ሀይደር ሸረፋ፣ መሐመድ አበራ እና ዳዊት ተፈራ ፣ ራምኬል ጀምስ እና ዲቫይን ዋቹኩዋ ከኢትዮጵያ ቡና፣ የሃዋሳ ከተማው ዓሊ ሱሌይማን እና የመቻሉ ሽመልስ በቀለ በእጩነት ቀርበዋል።   በኮከብ ወጣት ተስፈኛ ተጨዋች ዘርፍ በረከት ካሌብ ከኢትዮጵያ መድን፣ ይታገሱ ታሪኩ ከኢትዮጵያ ቡና፣ ሄኖክ ዮሐንስ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ ሄኖክ ይበልጣል ከባህር ዳር ከተማ እና ዘረሰናይ ብርሃነ ከመቀሌ 70 እንደርታ እጩዎች ዝርዝር ውስጥ ተካትዋል። አቡበከር ኑራ ከኢትዮጵያ መድን፣ ዳንላንድ ኢብራሂም ከኢትዮጵያ ቡና እና ፔፔ ሰዒዶ ከባህር ዳር ከተማ የኮከብ ግብ ጠባቂ እጩዎች ናቸው።   ተመልካቾች በተለያየ ዘርፍ የቀረቡትን ተጫዋቾች እስከ ሰኔ 13 ቀን 2017 ዓ.ም መምረጥ እና በ https://t.me/ethiopianlea የአክሲዮን ማህበሩ የቴሌግራም ገጽ ድምጽ መስጠት እንደሚችሉ ገልጿል። ከተመልካቾች ድምጽ በተጨማሪ አሰልጣኞች፣ ጋዜጠኞችና የሊጉን ጨዋታ የቀጥታ ስርጭት መብት የወሰደው የደቡብ አፍሪካው ሱፐር ስፖርት የቴሌቪዥን ጣቢያ በድምጽ አሰጣጡ ድርሻ እንዳላቸው ማህበሩ ገልጿል። በ2016 ዓ.ም በተካሄደው ምርጫ ጋናዊው ባሲሩ ዑመር ኮከብ ተጫዋች፣ ቢኒያም አይተን ኮከብ ተስፈኛ ተጫዋች እና ፍሬው ጌታሁን ኮከብ ግብ ጠባቂ ተብለው መመረጣቸው የሚታወስ ነው።
ባህር ዳር ከተማ በወንደሰን በለጠ ሀትሪክ ታግዞ ከአምስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Jun 12, 2025 86
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2017 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት ጨዋታ ባህር ዳር ከተማ ወላይታ ድቻን 4 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አጥቂው ወንደሰን በለጠ በ49ኛው፣ 64ኛው እና 67ኛው ደቂቃ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ወንደሰን በለጠ በ20ኛ ሳምንት የሊጉ መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን 4 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ ላይም ሀትሪክ መስራቱ የሚታወስ ነው። ተጫዋቹ በሁለቱም ጨዋታዎች ላይ ሀትሪክ የሰራው በሁለተኛው 45 ባስቆጠራቸው ግቦች መሆኑ አጋጣሚውን የተለየ ያደርገዋል። ፍጹም ዓለሙ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ባህር ዳር ከተማ በሊጉ ከአምስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል። ሶስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ቡድኑ ነጥቡን ወደ 51 ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በሊጉ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ወላይታ ድቻ በ45 ነጥብ 8ኛ ደረጃን ይዟል። ቀን ላይ በተደረገ ጨዋታ ሲዳማ ቡና እና ድሬዳዋ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ35ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ከሰኔ 7 ቀን 2017 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳል።
የፕሪሚየር ሊጉ 34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል
Jun 12, 2025 93
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳሉ። በወጣው መርሃ ግብር መሰረት ሲዳማ ቡና ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ይጫወታሉ። ሲዳማ ቡና በ46 ነጥብ 6ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ማሸነፍ ቡድኑ ከሁለት ተከታታይ ሽንፈት በኋላ ወደ አሸናፊነት እንዲመለስ ያደርገዋል። ድሬዳዋ ከተማ በ39 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ለመራቅ ለሚያደርገው እንቅስቃሴ ስንቅ የሚሆነው ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያገኛል። የ34ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር በወላይታ ድቻ እና ባህር ዳር ከተማ መካከል ምሽት 12 ሰዓት ላይ ይደረጋል። ወላይታ ድቻ በ45 ነጥብ 8ኛ ደረጃን ይዟል። ማሸነፍ ለቡድኑ በሊጉ ተከታታይ ድሉን እንዲያስመዘገብ ያስችለዋል። ባለፉት አምስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ድል ያልቀናው ባህር ዳር ከተማ በ48 ነጥብ 3ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ማሸነፍ ቡድኑን ወደ ድል ጎዳና ይመልሰዋል። ሁለቱ መርሃ ግብሮች ሲዳማ ቡና እና ወላይታ ድቻ ሰኔ 1 ቀን 2017 ዓ.ም በነበራቸው የኢትዮጵያ ዋንጫ የፍጻሜ ጨዋታ ምክንያት ወደ ዛሬ መዘዋወራቸውን የሊጉ አክሲዮን ማህበር በመረጃው አመልክቷል።
የ35ኛ ሳምንት የሊጉ መርሃ ግብር ላይ ማሻሻያ ተደረገ 
Jun 11, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 4/2017 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ35ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ላይ ማሻሻያ ማድረጉን የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታወቀ። ማሻሻያው የክለቦችን ውጤት እና የመጫወቻ ሜዳዎች ያሉበትን ሁኔታ ከግምት ውስጥ ያስገባ መሆኑን ገልጿል። በዚህም መሰረት እሁድ ሰኔ 8 ቀን 2017 ዓ.ም ይደረጉ የነበሩ የሊጉ ጨዋታዎች ወደ ቅዳሜ ሰኔ 7 ቀን 2017 ዓ.ም የተሳቡ ሲሆን እሁድ ሰኔ 8 ቀን 2017 ዓ.ም ደግሞ ነጥባቸው ከ39 በታች የሆኑ ሶስት ክለቦች ጨዋታዎች በተመሳሳይ ሰዓት በተለያዩ ሜዳዎች ይደረጋሉ። አዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ለምርቃት ዝግጅት የሚፈለግ በመሆኑ የሊጉ 35ኛ ሳምንት ቀሪ ጨዋታዎችም ሰኞ እና ማክሰኞም በወንጂ ሁለገብ ስታዲየም እንደሚቀጥሉ ማህበሩ ገልጿል። የ34ኛ ሳምንት ቀሪ ጨዋታዎችን ውጤት መሰረት በማድረግ ተጨማሪ አራተኛ ሜዳ ጥቅም ላይ ሊውል እንደሚችልም አመልክቷል። ውጤቶችን መሰረት በማድረግ የ35ኛ እና የ36ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ላይ ለውጥ ሊደረግ እንደሚችል የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቆ ነበር።
አካዳሚው ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር ተቀናጅቶ በመስራት የስፖርት ዘርፉን ለማሳደግ እያገዘ ነው
Jun 11, 2025 81
ሀዋሳ፤ ሰኔ 4/2017 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር ተቀናጅቶ በመስራቱ የስፖርት ዘርፉን ለማሳደግ እያገዘ መሆኑን የስፖርት ሳይንስ ምሁራን ገለጹ። የስፖርት ሳይንስ ምሁራኑ እንዳሉት የስፖርት ዘርፉን ውጤታማ ለማድረግ ውድድሮችንና ስልጠናዎችን በሳይንሳዊ መንገድ መምራት ይገባል። ለዚህም የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር የጀመረው ቅንጅታዊ ስራም ዘርፉን ውጤታማ ለማድረግ ያግዛል ብለዋል። በባህዳር ዩኒቨርሲቲ የስፖርት ሳይንስ መምህርና ተመራማሪ (ዶ/ር) ደምስ ጋሹ፤ ስፖርት አካዳሚው ባለፉት አመታት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር በመቀናጀት ከምልመላ እስከ ስልጠና ያሉ ተግባራት ለዘርፉ ስኬት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። አካዳሚው ከባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በጋራ ለመስራት ስምምነት መፈራረሙን የጠቀሱት ተመራማሪው ይህም በቀጣይ በስፖርት ዘርፉ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስፖርት ሳይንስ መምህሩ (ዶ/ር) ዘሩ በቀለ በበኩላቸው ለእግር ኳስ ሰልጣኞች የተዘጋጀ ረቂቅ የምልመላና ምዘና አተገባበር የጥናት ሰነድ ማቅረባቸውን ገልጸዋል። ከ2012 ጀምሮ ጥናት የተደረገበት ሰነዱ የተደራጀና ወጥነት ያለው የምልመላና ምዘና አሰራር ለመዘርጋት የሚያስችልና ቅንጅታዊ አሰራርን የሚጠይቅ ነው ብለዋል። አካዳሚው በዘርፉ ያሉ ችግሮችን በሳይንሳዊ መንገድ ለመፍታት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ክልሎች ጋር በቅንጅት መስራቱ በየአካባቢው ያለውን አቅም ለመለየት እንደሚያስችለውም ተናግረዋል።   የወለጋ ዩኒቨርሲቲ የስፖርት ሳይንስ መምህር ደስታ ፍቃዱ፤ አካዳሚው ከትምህርት ተቋማት ጋር በቅንጅት መስራቱ የሰው ሀብቱን በተገቢው ለመጠቀም ያስችለዋል ብለዋል። የዩኒቨርሲቲ ምሁራንም ተግባር ተኮር ትምህርት ላይ በማተኮር የዘርፉን ችግሮች መቅረፍ እንዳለባቸው ገልጸዋል። ከአካዳሚው ጋር በቅርበት በመስራት በእግር ኳስ፣ በአትሌቲክስና በፓራ ኦሎምፒክ ውጤታማ ተግባር ማከናወናቸውን የገለጹት ደግሞ በአትሌት ጥሩነሽ ዲባባ አትሌትክስ ማሰልጠኛ ማእከል የአትሌቶች ትምህርትና ስልጠና መሪ ስራ አስፈጻሚ ኢንስትራክተር ገረመው ፈጠነ ናቸው።   በኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ የጥናት፣ ምርምርና ማማከር አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር (ዶ/ር) አመንሲሳ ከበደ በበኩላቸው አካዳሚው ከሀረማያ፣ ጅማ፣ ሀዋሳ፣ ባህር ዳር፣ መቀሌና አዲሰ አበባ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በጋራ ለመስራት ስምምነት መፈራረሙን ተናግረዋል። በቀጣይ በየክልሉ ከአንድ ዩኒቨርሲቲ ጋር ስምምነት የሚያደርግ ሲሆን በስልጠና ማኑዋል ቀረጻ፣ የሰው ሀይልንና ሀብትን በጋራ በመጠቀም፣ የስልጠና ሂደቱን በሳይንሳዊ መንገድ ለመደገፍ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።   በየአመቱ የሚደረጉ የጥናትና ምርምር ውጤቶችም በዘርፉ ያሉ ችግሮችን እንዲቀርፉ በቅንጅት እንደሚሰራ ተናግረዋል። በዘንድሮው አመታዊ ጉባኤም ከተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የዘርፉ ምሁራን በጥናት መሳተፋቸውን ገልጸው በእግር ኳስ ላይ ትኩረት መደረጉንም ገልጸዋል።  
ፋሲል ከነማ በበረከት ግዛው ጎል ጣፋጭ ሶስት ነጥብ አግኝቷል
Jun 10, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2017(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ፋሲል ከነማ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በረከት ግዛው በ85ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ፋሲል ከነማ በ41 ነጥብ ደረጃውን ከ14ኛ ወደ 11ኛ ከፍ አድርጓል። ከስምንት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል። በሊጉ 9ኛ ድሉን ያሳካው ቡድኑ ከመውረድ ስጋቱ በመጠኑም ቢሆን እፎይታ አግኝቷል። በሊጉ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ38 ነጥብ ከ13ኛ ደረጃ ወደ 14ኛ ዝቅ ብሏል። ፋሲል ከነማ ቀሪ የሊግ ጨዋታዎቹን ላለመውረድ እየታገለ ካለው አዳማ ከተማ እና ሲዳማ ቡና ጋር ያደርጋል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ ቀሪ ጨዋታዎቹን ከመቻል እና ወራጅ ቀጠና ከሚገኘው መቀሌ 70 እንደርታ ጋር ያካሂዳል። ቀሪ ጨዋታዎቹ የክለቦቹን በሊጉ የመቆየት እና ያለመቆየት እጣ ፈንታ ይወስናሉ። ቀን ላይ በተደረገ ጨዋታ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን መቻልን 2 ለ 0 ረቷል።
የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን ከመቻል ጋር ይጫወታል 
Jun 10, 2025 60
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2017(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከጨዋታዎቹ ትኩረትን የሳበው ኢትዮጵያ መድን እና መቻል ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም የሚካሂዱት ጨዋታ ነው። ኢትዮጵያ ቡና ትናንት ነጥብ መጣሉን ተከትሎ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን ሶስት ጨዋታዎች እየቀሩት ለመጀመሪያ ጊዜ ዋንጫውን ማንሳቱን አረጋግጧል። መድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ይሳተፋል። መርሃ ግብሩ በአሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ የሚመራው ቡድን ዋንጫውን ማንሳቱን ማረጋገጡን ተከትሎ የሚያደርገው ጨዋታ ነው። ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀው መቻል በ44 ነጥብ 9ኛ ደረጃን ይዟል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ፋሲል ከነማ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ፋሲል ከነማ በተመሳሳይ 38 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው 13ኛ እና 14ኛ ደረጃን ይዘዋል። ማሸነፍ የመውረድ ስጋት ላለባቸው ሁለቱ ክለቦች ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝላቸዋል።
ኢትዮጵያ መድን የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ ማንሳቱን አረጋገጠ 
Jun 9, 2025 87
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 2/2017 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ መድን የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዋንጫን ለመጀመሪያ ጊዜ ማንሳቱን አረጋግጧል። ዛሬ ረፋድ ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደ የ34ኛ ሳምንት ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ ቡና አንድ አቻ ተለያይተዋል። ዩጋንዳዊው ጂኦፍሪ ዋሳዋ በ54ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ኢትዮጵያ ቡናን መሪ አድርጓል። ይሁንና መሉጌታ ወልደጊዮርጊስ በ64ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ግብ መቀሌ 70 እንደርታን አቻ አድርጋለች።   ኢትዮጵያ ቡና ነጥብ መጣሉን ተከትሎ ኢትዮጵያ መድን ሶስት ጨዋታዎች እየቀሩት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዋንጫን ለመጀመሪያ ጊዜ ማንሳቱን አረጋግጧል። በአሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ የሚመራው ኢትዮጵያ መድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ ይሳተፋል። ኢትዮጵያ ቡና በ56 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። መቀሌ 70 እንደርታ በ38 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ከሰዓትም ቀጥሎ ሲውል ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሀድያ ሆሳዕና ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
መውረድ የሚያሰጋቸው ክለቦች የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ 
Jun 9, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 2/2017 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። የዕለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ ቡናን ከጠዋቱ 3 ሰዓት ከ30 ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ያገናኛል። መቀሌ 70 እንደርታ በ37 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ማሸነፍ ላለመውረድ እያደረገ ላለው ትግል ወሳኝ ሶስት ነጥብ እንዲያገኝ ያስችለዋል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና በ55 ነጥብ 2ኛ ደረጃን ይዟል። ቡናማዎቹ ማሸነፍ በሊጉ ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል እንዲመለስ ያደርገዋል። ቡድኑ ከተሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን ዋንጫውን ማንሳቱን ያረጋግጣል። ቀን 9 ሰዓት ላይ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሃዋሳ ከተማ ይጫወታሉ። ከሊጉ የወረደው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ19 ነጥብ የመጨረሻውን 18ኛ ደረጃን ይዟል። ሃዋሳ ከተማ በ44 ነጥብ 7ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት 10 የሊግ ጨዋታዎች አልተሸነፈም። በዕለቱ የመጨረሻ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ሀድያ ሆሳዕና ምሽት 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። የአምናው የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ40 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ማሸነፍ ቡድኑ ከስምንት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት እንዲመለስ እና ከወራጅ ቀጠና ክልል እንዲርቅ ያስችለዋል። በ44 ነጥብ 9ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠው ሀድያ ሆሳዕና ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። ሶስት ነጥብ የሀድያ ሆሳዕናን ደረጃን በጊዜያዊነት ወደ 4ኛ ከፍ ያደርጋል።
ፖርቹጋል ስፔንን በማሸነፍ የዩኤፋ ኔሽንስ ሊግ ዋንጫ አነሳች
Jun 8, 2025 86
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 1/2017 (ኢዜአ)፦ በዩኤፋ ኔሽንስ ሊግ ኤ ሻምፒዮንሺፕ የፍጻሜ ጨዋታ ፖርቹጋል ስፔንን በመለያ ምት በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ማምሻውን በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኑኖ ሜንዴዝ እና ክርስቲያኖ ሮናልዶ ለፖርቹጋል ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ማርቲን ዙቢሜንዲ እና ማይክል ኦያርዛባል ለስፔን ግቦቹን አስቆጥረዋል።   ጨዋታው በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሁለት አቻ በመጠናቀቁ ተጨማሪ 30 ደቂቃ ተጨምሯል። በጭማሪ ሰዓትም ግብ ባለመቆጠሩ ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቷል። በዚህም ፖርቹጋል ስፔንን 5 ለ 3 በማሸነፍ የኔሽንስ ሊግን ዋንጫን ለሁለተኛ ጊዜ አንስታለች። ከስፔን በኩል አልቫሮ ሞራታ ፍጹም ቅጣት ምት ስቷል። ውድድሩን ለሁለት ጊዜ በማሸነፍ የመጀመሪያዋ ሀገር ሆናለች። ቡድኑ እ.አ.አ 2019 ውድድሩ ሲጀመር የመጀመሪያው አሸናፊ ነበረች። ለውድድሩ ፍጻሜ ለሶስት ተከታታይ ጊዜ ለፍጻሜ የደረሰችው ስፔን ዋንጫውን ሳታገኝ ቀርታለች። የዋንጫ ክብሯንም ማስጠበቅ አልቻለችም። ቀን ላይ በተደረገ ጨዋታ ፈረንሳይ ጀርመንን በኪሊያን ምባፔ እና ማይክል ኦሊሴ ግቦች 2 ለ 0 በማሸነፍ በውድድሩ ሶስተኛ ደረጃ ይዛ አጠናቃለች።
አዳማ ከተማ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል 
Jun 8, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 1/2017 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት ጨዋታ አዳማ ከተማ ስሑል ሽሬን 4 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቢንያም አይተን ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አድናን ረሻድ እና የስሑል ሽሬው ሰለሞን ገብረክርስቶስ በራሱ ግብ ላይ ቀሪዎቹን ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ብርሃኑ አዳሙ እና አላዛር ሽመልስ ለስሑል ሽሬ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አዳማ ከተማ በሊጉ አራተኛ ተከታታይ ድሉን አስመዝግቧል። በ38 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ቢገኝም አሁንም ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ 13ኛ ደረጃ ላይ ከሚገኘው ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና 14ኛ ደረጃን ከያው ፋሲል ከነማ ጋር በነጥብ እኩል ሆኗል። በአንጻሩ ከሊጉ የወረደው ስሑል ሽሬ በ22 ነጥብ 17ተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ 16ኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በሊጉ ላለመውረድ እየተደረገ ያለው ፋክክር የበለጠ አጓጊ ሆኗል። ቀን ላይ በተደረገ የ34ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ አርባምንጭ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም