ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የአፍሪካ እግር ኳስ ኃያላኑ ኮትዲቯር እና ካሜሮን የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Dec 28, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ)፦ የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሁለተኛ መርሃ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። በዕለቱ የምድብ አምስት እና ስድስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በምድብ ስድስት የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ ባለቤት ኮትዲቭዋር ከአምስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ካሜሮን ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በማራካሽ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ የእግር ኳስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ ኮትዲቭዋር ሞዛምቢክን፣ ካሜሮን ጋቦንን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ሁለቱ የአፍሪካ እግር ኳስ ኃያላን በአህጉራዊው መድረክ ሲገናኙ የአሁኑ ለስድስተኛ ጊዜ ነው። ሀገራቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገናኙት ሱዳን እ.አ.አ በ1970 ባዘጋጀችው ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በወቅቱ ካሜሮን 3 ለ 2 አሸንፋለች። እ.አ.አ በ1992 በሴኔጋል በተካሄደው 18ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በግማሽ ፍጻሜ ባደረጉት ጨዋታ ኮትዲቭዋር ካሜሮንን በመለያ ምት በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፋለች። ኮትዲቭዋር በፍጻሜው ጋናን በማሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ አንስታለች። ቡድኖቹ ለመጨረሻ ጊዜ በአህጉራዊው መድረክ የተገናኙት ኢኳቶሪያል ጊኒ እ.አ.አ በ2015 ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በምድብ አራት በተደረገው ጨዋታ ኮትዲቭዋር በማክስ-አለን ግራዴል ጎል 1 ለ 0 አሸንፋለች። በአጠቃላይ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫው አምስት ጊዜ ተገናኝተው ካሜሮን ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ ኮትዲቭዋር ሁለት ጊዜ ድል ቀንቷታል። ኮትዲቭዋር የዘንድሮውን ጨምሮ ለ26ኛ ጊዜ እየተሳተፈች የምትገኝ ሲሆን ሁለት ጊዜ ዋንጫውን አንስታለች። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ናት። በአንጻሩ ለ22ኛ ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫው የተሳተፈችው ካሜሮን አምስት ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ ከግብጽ በመቀጠል ስኬታማዋ ሀገር ናት። በአፍሪካ እግር ኳስ ደማቅ ታሪክ ያላቸው ሁለቱ ሀገራት በጨዋታው ላይ ጠንካራ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። ጨዋታውን የሚያሸንፈው ቡድን ወደ ጥሎ ማለፍ ይገባል። በምድብ ስድስት ሌላኛው መርሃ ግብር ጋቦን ከሞዛምቢክ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 በአጋዲር ስታዲየም ይጫወታሉ። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያ ጨዋታ ካስተናገዱት ሽንፈት በኋላ የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። በተያያዘም የምድብ አምስት ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ አልጄሪያ ከቡርኪናፋሶ በሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም ይጫወታሉ። በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ አልጄሪያ ሱዳንን 3 ለ 0፣ ቡርኪናፋሶ ኢኳቶሪያል ጊኒን 2 ለ 1 አሸንፈዋል። በሌላኛው የምድቡ መርሃ ግብር ኢኳቶሪያል ጊኒ ከሱዳን ምሽት 12 ሰዓት ላይ በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ ስምንተኛ ቀኑን ይዟል።
ናይጄሪያ ጥሎ ማለፉን ተቀላቀለች
Dec 28, 2025 61
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት ጨዋታ ናይጄሪያ ቱኒዚያን 3 ለ 2 አሸንፋለች። ማምሻውን በፌዝ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቪክቶር ኦሲሜን፣ ዊልፍሬድ ንዲዲ እና አዴሞላ ሉክማን የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሞንታሳር ታልቢ በጨዋታ እና አሊ አብዲ በፍጹም ቅጣት ምት ለቱኒዚያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጨዋታው አዝናኝ እና ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ናይጄሪያ በስድስት ነጥብ ግብጽን ተከትሎ ጥሎ ማለፍ የገባች ሁለተኛዋ ሀገር ሆናለች። የመጀመሪያ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ቱኒዚያ በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ምድብ ዛሬ በተደረገ ጨዋታ ዩጋንዳ እና ታንዛንያ አንድ አቻ ተለያይተዋል። የምድብ ሶስት የመጨረሻ መርሃ ግብር ማክሰኞ ታህሳስ 21 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ዩጋንዳ ከናይጄሪያ እና ታንዛንያ ከቱኒዚያ ጋር ይጫወታሉ።
በምስራቅ አፍሪካ ደርቢ ዩጋንዳ እና ታንዛንያ አቻ ተለያዩ
Dec 27, 2025 108
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት መርሃ ግብር ዩጋንዳ እና ታንዛኒያ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በአል መዲና ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሳይመን ምሱቫ በ59ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠረው ጎል ታንዛንያን መሪ አድርጓል። ኡቼ ኢክፒዙ በ80ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፈው ግብ ዩጋንዳ አቻ ሆናለች። የዩጋንዳው አለን ኦኬሎ በ91ኛው ደቂቃ የሳተው የፍጹም ቅጣት ምት ሀገሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ እንዳታገኝ አድርጓታል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ዩጋንዳ እና ታንዛኒያ በምድቡ የመጀመሪያ ነጥባቸውን አግኝተዋል። በዚሁ ምድብ ናይጄሪያ ከቱኒዚያ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በፌዝ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
በተጠባቂው ጨዋታ አስቶንቪላ ቼልሲን በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Dec 27, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አስቶንቪላ ከመመራት ተነስቶ ቼልሲን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆአኦ ፔድሮ በ37ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ቼልሲ መሪ ሆኖ ቆይቷል። ከእረፍት መልስ ኦሊ ዋትኪንስ በ63ኛው እና በ84ኛው ደቂቃ ያስቆጠራቸው ግቦች አስቶንቪላን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አስጨብጧል። በሊጉ ስምንተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው አስቶንቪላ በ39 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቼልሲ በ29 ነጥብ ከነበረበት አራተኛ ደረጃ ወደ አምስተኛ ዝቅ ብሏል። በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ19ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አስቶንቪላ ከሊጉ መሪ አርሰናል ማክሰኞ ታህሳስ 21 ቀን 2018 ዓ.ም በኤምሬትስ ስታዲየም የሚያደርገው ጨዋታ በጉጉት ይጠበቃል።
በተጠባቂው ጨዋታ ሴኔጋል እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ነጥብ ተጋሩ
Dec 27, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አራት መርሃ ግብር ሴኔጋል እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በታንጀር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሴድሪክ ባካምቡ በ61ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን መሪ አድርጓል። ሳዲዮ ማኔ በ69ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፋት ግብ ሴኔጋል አቻ ሆናለች። የሁለቱ ብሄራዊ ቡድኖች ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ሴኔጋል እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በምድብ አራት በተመሳሳይ አራት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። በዚሁ ምድብ ዛሬ በተደረገ ጨዋታ ቤኒን ቦትስዋናን 1 ለ 0 አሸንፋለች። በምድቡ የመጨረሻ መርሃ ግብር ማክሰኞ ታህሳስ 21 ቀን 2018 ዓ.ም ቤኒን ከሴኔጋል እና ቦትስዋና ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ ወደ ጥሎ ማለፍ የሚገቡ ሀገራት የሚለዩባቸው ናቸው።
አርሰናል የሊጉን መሪነት ዳግም ተረከበ
Dec 27, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ18ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርሰናል ብራይተንን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማርቲን ኦዴጋርድ እና የብራይተኑ ጆርጂኒዮ ሩተር በራሱ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዲያጎ ጎሜዝ ለብራይተን ብቸኛውን ጎል ከመረብ አሳርፏል። በሊጉ 13ኛ ድሉን ያስመዘገበው አርሰናል በ42 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከማንችስተር ሲቲ ዳግም ተረክቧል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ብራይተን በ24 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በሌሎች ጨዋታዎች ሊቨርፑል በራያን ግራቨንበርች እና ፍሎሪያን ዊትዝ ግቦች ዎልቭስን 2 ለ 1 ሲያሸንፍ ሳንቲያጎ ቡዌኖ ለዎልቭስ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ብሬንትፎርድ ፉልሃምን 4 ለ 1፣ ፉልሃም ዌስትሃምን 1 ለ 0 ሲያሸንፍ በርንሌይ ከኤቨርተን ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ቼልሲ ከአስቶንቪላ በቪላ ፓርክ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ቤኒን በአፍሪካ ዋንጫው የመጀመሪያ ድሏን አስመዘገበች
Dec 27, 2025 71
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አራት ጨዋታ ቤኒን ቦትስዋናን 1 ለ 0 አሸንፋለች። በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዮሃን ሮቼ በ28ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ላይ ቤኒን ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ማንችስተር ሲቲ ኖቲንግሃም ፎረስትን በማሸነፍ የሊጉ መሪ ሆነ በውድድሩ የመጀመሪያ ድሏን ያስመዘገበችው ቤኒን በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። በአንጻሩ ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ቦትስዋና ያለ ምንም ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። በዚሁ ምድብ ሴኔጋል ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በታንጀር ስታዲየም ይጫወታሉ።
ማንችስተር ሲቲ ኖቲንግሃም ፎረስትን በማሸነፍ የሊጉ መሪ ሆነ
Dec 27, 2025 68
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ኖቲንግሃም ፎረስትን 2 ለ 1 አሸንፏል። በሲቲ ግራውንድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቲጃኒ ራይንደርስ እና ራያን ቼርኪ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኦማሪ ሁትቺንሰን ለኖቲንግሃም ፎረስት ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ 13ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ በ40 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከአርሰናል በጊዜያዊነት ተረክቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኖቲንግሃም ፎረስት በ18 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። አርሰናል ምሽት 12 ሰዓት ላይ ከብራይተን የሚያደርገው ጨዋታ ይጠበቃል። መድፈኞቹ ካሸነፉ የሊጉን መሪነት መልሰው ይረከባሉ።
ከለውጡ መንግሥት ወዲህ በስፖርቱ ዘርፍ መነቃቃት የፈጠሩ በርካታ ሥራዎች ተከናውነዋል
Dec 27, 2025 121
ሐረር፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡- ከለውጡ መንግሥት ወዲህ በስፖርቱ ዘርፍ መነቃቃት የፈጠሩ በርካታ ሥራዎች መከናወናቸውን የሐረሪ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙራድ አብዲ አስገነዘቡ። የስፖርት ብልጽግና እውን እንዲሆን የዘርፉ ማንሰራራት ጉዞ በሚል መሪ ሐሳብ ሕዝባዊ ውይይት ተካሂዷል። በዚሁ ወቅት ኮሚሽነሩ እንዳሉት፤ በስፖርቱ ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት በሕዝቡ የተቀናጀ ተሳትፎ ተጠናክረው ይቀጥላሉ። ከለውጡ ወዲህ በስፖርቱ ዘርፍ መነቃቃት የፈጠሩ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቁመው፤ መንግሥት ስፖርቱን በበጀት በመደገፍ፣ የስፖርት ማዘውተርያ ስፍራዎችን የማልማት ሥራ ማከናወኑን አስገንዝበዋል። ስፖርቱን ከቱሪዝም ዘርፍ በማስተሳሰር ምቹ ሁኔታ የመፍጠር ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው፤ የማዘውተሪያ ስፍራዎችን የመጠበቅና የማልማት ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። በማንሰራራት ላይ የሚገኘውን ስፖርት ሕዝባዊ መሰረት እንዲኖረው በቁርጠኝነት መሥራት ይጠበቃል ያሉት ደግሞ በብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ጃፈር ሱፍያን ናቸው። የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው፤ የክልሉ መንግሥት ለስፖርት ዘርፍ መጎልበት እያከናወነ ላለው ጥረት አመሥግነዋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ተስተካካይ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሲዳማ ቡናን በሰፊ የግብ ልዩነት አሸነፈ
Dec 27, 2025 65
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሲዳማ ቡናን 5 ለ 0 ረትቷል። በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ተስተካካይ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሸገር ከተማን አሸነፈ በአበበ በቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ንግስት በቀለ ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር እሙሽ ዳንኤል፣ መሳይ ተመስገን እና ረድኤት አስረሳኸኝ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሊጉ 10ኛ ድሉን ያስመዘገበው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ32 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ዝቅ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሲዳማ ቡና በ18 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። የቡድኖቹ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ በነበረው ተሳትፎ ምክንያት የተራዘመ ነው። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በያዝነው ሳምንት የመጀመሪያ ተስተካካይ ጨዋታውን ከሸገር ከተማ አድርጎ 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ዙር መርሃ ግብር መጠናቀቁ ይታወቃል።
ውድድሩ የከተማዋን ነዋሪዎች ማህበራዊ ትስስር ለማጎልበት ያግዛል
Dec 27, 2025 69
ነቀምቴ ፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡- በምሥራቅ ወለጋ ዞን ነቀምቴ ከተማ በተካሄደው ስፖርት ለሰላም ውድድር የከተማዋ ነዋሪዎች ማህበራዊ ትስስራቸውን ለማጎልበት ያላቸውን ጽኑ ፍላጎት ማሳየታቸው ተገለጸ፡፡ በኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን እና በነቀምቴ ከተማ አስተዳደር አስተባባሪነት የስፖርት ለሰላም የሩጫ ውድድር ዛሬ በነቀምቴ ከተማ ተካሂዷል። በመርሃ ግብሩ ላይ በኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ረዳት ኮሚሽነር አትሌት ማርቆስ ገነቲ፣ የምሥራቅ ወለጋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ወጋሪ ነገራ፣ የነቀምቴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ መሰረት ሀይሉ ፣ የወለጋ ዩኒቨርስቲ መምህራን እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል። ሩጫውን ያስጀመረው የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ረዳት ኮሚሽነር አትሌት ማርቆስ ገነቲ ባስተላለፈው መልዕክት፤ የሰላም ሩጫው የተካሄደው ሰላምን ለማፅናት በሚደረገው ጥረት የሕብረተሰቡን የጎላ ተሳትፎ ለማስገንዘብ ነው ብሏል። በሰላም ሩጫውም ነዋሪዎቹ ሰላምን ጠብቆ ለማዝለቅ፣ ልማትን ለማስቀጠልና ማህበራዊ ትስስራቸውን ለማጎልበት ያላቸውን ጽኑ ፍላጎት ማሳየታቸውን ተናግሯል። የነቀምቴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ መሰረት ሀይሉ በበኩላቸው፤ አስተዳደሩ የሕግ የበላይነት በማስከበር ሰላምን በማፅናት የሕብረተሰቡን የመሰረተ ልማት ፍላጎት ለማሟላት አበክሮ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ የተካሄደው የሰላም ሩጫም በአካባቢው ያለውን ሰላምና ልማትን አጉልቶ ያንጸባረቀ መሆኑን ገልጸዋል። ከተማዋ በፈጣን የእድገት ጎዳና ላይ ናት ያሉት ከንቲባው፤ ይህንን እውነታ ለማሳየት የሰላም ሩጫው የማይተካ ድርሻ አለው ብለዋል። የነቀምቴ ከተማና አካባቢው ነዋሪዎች በሰላም ሩጫው በመሳተፍ ከመንግስት ጋር በመቀናጀት ልማትና ሰላምን ለማፅናት ያላቸውን ቁርጠኝነት በድጋፍ ማረጋገጣቸውን አንስተዋል። 10 ኪሎ ሜትር በሸፈነው ሩጫ ላይ የተሳተፈችው ከኦሮሚያ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ዋና ሳጅን አትሌት ጉተኒ ሻንቆ ፤ በወለጋ አካባቢ ያለውን ሰላምና ልማት በማድነቅ የሚበረታታ መሆኑን ተናግራለች። ዛሬ የተካሄደው ስፖርታዊ ውድድር የአካባቢውን ትክክለኛ ገጽታ ለማሳየት እንደሚያግዝም ጠቁማለች።
የሊጉ መሪ አርሰናል ከብራይተን ጋር ይጫወታል
Dec 27, 2025 93
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሰባት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በ"ቦክሲንግ ደይ" መርሃ ግብ ማንችስተር ዩናይትድ ኒውካስትል ዩናይትድን አሸነፈ በአፍሪካ ዋንጫ ናይጄሪያ ከቱኒዚያ ሴኔጋል ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ ምሽት 12 ሰዓት ላይ አርሰናል ብራይተንን በኤምሬትስ ስታዲየም ያስተናግዳል። አርሰናል ሊጉን በ39 ነጥብ እየመራ ነው። ብራይተን በ24 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ኖቲንግሃም ፎረስት ከማንችስተር ሲቲ በሲቲ ግራውንድ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኖቲንግሃም ፎረስት በ18 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ በ37 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አርሰናል እና ማንችስተር ሲቲ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች በተመልካቾች ትኩረትን አግኝተዋል። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ቼልሲ ከአስቶንቪላ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታም ይጠበቃል። ቼልሲ በ29 ነጥብ አራተኛ እና አስቶንቪላ በ36 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ሊቨርፑል ከዎልቭስ፣ ዌስትሃም ዩናይትድ ከፉልሃም፣ ብሬንትፎርድ ከቦርንማውዝ እና በርንሌይ ከኤቨርተን በተመሳሳይ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በአፍሪካ ዋንጫ ናይጄሪያ ከቱኒዚያ ሴኔጋል ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Dec 27, 2025 68
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሰባተኛ ቀን ውሎ የምድብ ሶስት እና አራት ሁለተኛ ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ። በምድብ ሶስት ናይጄሪያ ከቱኒዚያ ምሽት አምስት ላይ በፌዝ ስታዲየም ይጫወታሉ። በምድቡ የመጀመሪያ ጨዋታዎች ናይጄሪያ ታንዛንያን 2 ለ 1 እና ቱኒዚያ ዩጋንዳን 3 ለ 1 አሸንፈዋል። ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለሰባተኛ ጊዜ ነው። የመጀመሪያ የአፍሪካ ዋንጫ ግንኙነታቸው ጋና እ.አ.አ በ1978 ባዘጋጀችው 11ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነበር። ቡድኖቹ በደረጃ ጨዋታ ተገናኝተው ናይጄሪያ በባባ ኦቱ መሐመድ ግቦች 2 ለ 0 በማሸነፍ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ሀገራቱ በአህጉራዊው መድረክ ለመጨረሻ ጊዜ እርስ በእርሳቸው የተጫወቱት ካሜሮን እ.አ.አ በ2022 ባዘጋጀችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በጥሎ ማለፍ ላይ ተገናኝተው ቱኒዚያ በዩሱፍ ምሳክኒ ጎል 1 ለ 0 በማሸነፍ ለሩብ ፍጻሜ አልፋለች። ናይጄሪያ እና ቱኒዚያ በአፍሪካ ዋንጫው ባደረጓቸው ስድስት ጨዋታዎች ናይጄሪያ አራት ጊዜ ስታሸንፍ ቱኒዚያ ሁለት ጊዜ ድል ቀንቶታል። የሚያሸንፈው ቡድን ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቱን ያረጋግጣል። ናይጄሪያ የአፍሪካ ዋንጫን ሶስት ጊዜ፣ ቱኒዚያ አንድ ጊዜ አሸንፈዋል። በምድብ አንድ ሌላኛው መርሃ ግብር ዩጋንዳ ከታንዛንያ ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ በአል መዲና ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ብሄራዊ ቡድኖቹ በመጀመሪያ ጨዋታ ካስተናገዱት ሸንፈት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። በተያያዘም የምድብ አራት ጨዋታዎችም ዛሬ ይደረጋሉ። ሴኔጋል ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በታንጀር ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። በምድቡ የመጀመሪያ መርሃ ግብር ሴኔጋል ቦትስዋናን 3 ለ 0፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ቤኒን 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ሀገራቱ ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ዋንጫ ሁለት ጨዋታዎችን እርስ በእርስ አድርገዋል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1968 ባዘጋጀችው ስድስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ተገናኝተው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ 2 ለ 1 አሸንፋለች። ማሊ እ.አ.አ በ2002 ባዘጋጀችው 23ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሩብ ፍጻሜው ተገናኝተው ሴኔጋል 2 ለ 0 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። አሸናፊው ቡድን ጥሎ ማለፉን ይቀላቀላል። ሴኔጋል የአፍሪካ ዋንጫን አንድ ጊዜ ያነሳች ሲሆን ዴሞክራቲክ ኮንጎ ሁለት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሆናለች። በዚሁ ምድብ ቤኒን ከቦትስዋና ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሁለቱ ሀገራት የመጀመሪያ ድላቸውን ለማግኘት ይፋለማሉ።
በሴቶች ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሲዳማ ቡና ተስተካካይ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል
Dec 27, 2025 58
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሲዳማ ቡና ዛሬ ይጫወታሉ። ጨዋታው በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ይካሄዳል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 12 ጨዋታዎች በዘጠኙ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በሁለት ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 29 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ሶስት ጎሎችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ29 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በሊጉ 12 ጨዋታዎችን አድርጎ በአምስቱ ሲያሸንፍ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በ12ቱ ጨዋታዎች ላይ 14 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 12 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሲዳማ ቡና በ18 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዛሬውን ካሸነፈ ከሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ዝቅ ያደርጋል። በአንጻሩ ሲዳማ ቡና ድል ከቀናው ደረጃውን ከሰባተኛ ወደ ስድስተኛ ከፍ ያደርጋል። የቡድኖቹ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ በነበረው ተሳትፎ ምክንያት የተራዘመ ነው። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በያዝነው ሳምንት የመጀመሪያ ተስተካካይ ጨዋታውን ከሸገር ከተማ አድርጎ 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው።
ሞሮኮ እና ማሊ አቻ ተለያዩ
Dec 26, 2025 77
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 17/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አንድ ተጠባቂ ጨዋታ አዘጋጇ ሞሮኮ እና ማሊ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብራሂም ዲያዝ በመጀመሪያ አጋማሽ የባከኑ ደቂቃዎች ላይ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠራት ጎል ሞሮኮ መሪ ሆናለች። የሪያል ማድሪዱ የክንፍ መስመር ተጫዋች ዲያዝ በውድድሩ ላይ ሁለተኛ ግቡን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከእረፍት መልስ በ64ኛው ደቂቃ ማሊ ያገኘችውን የፍጹም ቅጣት ምት ያሲን ሲናዮኮ ወደ ግብ በመቀየር ማሊን አቻ አድርጓል። ሲናዮኮ በውድድሩ ላይ ሁለተኛ ግቡን አስቆጥሯል። ጨዋታው አካላዊ ሽኩቻ ያመዘነበት ሲሆን ሞሮኮ በተጋጣሚ ላይ አንጻራዊ ብልጫ ወስዳለች። ሞሮኮ ከ900 ደቂቃዎች በኋላ ግብ በኋላ ግብ ተቆጥሮባታል። የሪያል ማድሪዱ አጥቂ ኪሊያን ምባፔ የፒኤስጂ የቀድሞ የቡድን አጋሩን እና የሞሮኮውን ተጫዋች አሽራፍ ሀኪሚ እና ብሄራዊ ቡድኑን ለመደገፍ በስታዲየም ተገኝቶ ጨዋታውን ተከታትሏል። የምድብ አንድ መሪ ሞሮኮ ነጥቧን ወደ አራት ከፍ አድርጋለች። ማሊ ከሁለት ጨዋታ ሁለት ነጥብ በማግኘት ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚህ ምድብ ዛሬ በተደረገ ጨዋታ ዛምቢያ እና ኮሞሮስ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የምድብ አንድ የመጨረሻ ጨዋታዎች ሰኞ ታህሳስ 20 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳሉ። አዘጋጇ ሞሮኮ ከዛምቢያ እና ኮሞሮስ ከማሊ ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ ወደ ጥሎ ማለፍ የሚገቡ ቡድኖችን ይለያሉ።
ዛምቢያ እና ኮሞሮስ አቻ ተለያዩ
Dec 26, 2025 71
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 17/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አንድ ጨዋታ ዛምቢያ እና ኮሞሮስ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። የኮሞሮሱ የክንፍ መስመር ተጫዋች ማይዚያኔ ማኦሊዳ በ19ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ከጨዋታ ውጪ በመሆኑ ተሽሯል። በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ግብ ያልተቆጠረበት የመጀመሪያው ጨዋታ ሆኗል። ውጤቱን ተከትሎ ዛምቢያ በሁለት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። ኮሞሮስ በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። በምድብ አንድ አዘጋጇ ሞሮኮ ከማሊ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም የምታደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
የአፍሪካ ዋንጫ ኮከብ ተጫዋቾች
Dec 26, 2025 105
ከኢትዮጵያዊው ኮከብ መንግስቱ ወርቁ እስከ ናይጄሪያዊው ዊሊያም ትሮስት-ኤኮንግ፤ የአፍሪካ ዋንጫ ኮከብ ተጫዋቾች እ.አ.አ በ1957 የተጀመረው የአፍሪካ ዋንጫ የአህጉሪቷ ቁንጮ የእግር ኳስ መድረክ ሆኖ ለሰባት አስርት ዓመታት ጸንቶ ቆይቷል። ውድድሩ በአፍሪካ እግር ኳስ ያሉ ምርጥ ብሄራዊ ቡድኖች እና እምቅ ችሎታ ያላቸው ተጫዋቾች የሚታይዩበት ነው። አፍሪካ ዋንጫ ለሀገራት ዋንጫ ብቻ የሚሸልም መድረክ አይደለም በውድድሩ ድንቅ የግል ብቃታቸውን ላሳዩ ተጫዋቾች እውቅና እና ሽልማት ያበረክታል። ከሽልማቱ አንዱ የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች ሽልማት ነው። በ68 ዓመታት የውድድሩ ታሪክ የዘንድሮውን ሳይጨምር 34 ተጫዋቾች ኮከብ ተጫዋች በመባል ተመርጠዋል። የኮከብ ተጫዋች ሽልማት በውድድሩ ላይ ትልቅ ተጽእኖ የፈጠሩ እና ድንቅ ብቃታቸውን ያሳዩ ተጫዋቾች እውቅና የሚያገኙበት ነው። ከግብጻዊው መሐመድ ዲያብ አልታር (በቅጽል ስሙ አድ-ዲባ) አንስቶ እስከ ናይጄሪያዊው ዊሊያም ትሮስት-ኤኮንግ የግል ክብሩን ወስደዋል። ሱዳን እ.አ.አ በ1957 ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅ ነበረች። በውድድሩ ሱዳንን ጨምሮ ኢትዮጵያ እና ግብጽ ተሳትፈዋል። በውድድሩ የፍጻሜ ጨዋታ ላይ ግብጽ ኢትዮጵያን 4 ለ 0 አሸንፋለች። በፍጻሜው መሐመድ ዲያብ አልታር አራት ግቦችን አስቆጥሯል። በውድድሩ ታሪክ የመጀመሪያውን ሀትሪክ የሰራ እና ከአራት ግቦችን ያስቆጠረ ተጫዋች ሆኗል። አልታር በውድድሩ አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ከመሆኑ በተጨማሪ የውድድሩ የመጀመሪያው ኮከብ ተጫዋች ሆኖ ተመርጧል። ግብጽ እ.አ.አ በ1959 ራሷ አዘጋጅታ ራሷ ባነሳቸው ሁለተኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሀገሩ ዜጋ የሆነው መሐሙድ ኤል-ጎሃሪ ባሳየው ብቃት ኮከብ ተጫዋች ሆኖ ተመርጧል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1962 ባዘጋጀችው ሶስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ አጥቂው መንግስቱ ወርቁ የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች ሆኖ ተመርጧል። ይህም መንግስቱ ወርቁ በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ ኮከብ ተጫዋች የሆነ የተመረጠ ብቸኛው ኢትዮጵያዊ ያደርገዋል። ታዋቂው አጥቂ ኢትዮጵያ በፍጻሜው ጨዋታ ግብጽን 4 ለ 2 ያሸነፈችበትን ጨዋታ ላይ ያስቆጠራትን ጎል ጨምሮ በውድድሩ ላይ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። መንግስቱ ወርቁ ኢትዮጵያ ታሪካዊውን ዋንጫ እንድታነሳ ትልቁን ሚና ተጫውቷል። መንግስቱ ወርቁ በስድስት የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ 17 ጨዋታዎችን አድርጎ 10 ጎሎችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ከምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪዎች መካከል ይጠቀሳል። ካሜሮናዊው ሮጀር ሚላ እና ግብጻዊ አህመድ ሀሰን በአፍሪካ ዋንጫ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ ኮከብ ተጫዋች ሆነው ተመርጠዋል። ሮጀር ሚላ ግብጽ እ.አአ በ1986 ባዘጋጀችው 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያውን የኮከብ ተጫዋች ሽልማት አገኝቷል። ሀገሩ ካሜሮን በፍጻሜው በግብጽ ብትሸንፍም ሚላ ለካሜሮን ያበረከተው አስተዋጽኦ ወሳኝ የሚባል ነበር። አራት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ መሆንም ችሏል። ካሜሮናዊው አጥቂ እ.አ.አ በ1988 በሞሮኮ በተካሄደው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሀገሩ ዋንጫ እንድታነሳ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። ካሜሮን በፍጻሜው ናይጄሪያን በጄሮም ኩንቴ ግብ 1 ለ 0 ስታሸንፍ ተላፊ ነበር። በአጠቃላይ በውድድሩ ላይ ሁለት ግቦችን በማስቆጠር ከኮትዲቯሩ አብዱላዬ ትራኦሬ፣ ከአልጄሪያው ላክዳር ቤልሆሚ እና ከግብጹ ገማል አብደልሃሚድ ጋር በጋራ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኖ አስቆጥሯል። ሌላኛው ሁለት ጊዜ የኮከብ ተጫዋችነት ሽልማት ያገኘው ተጫዋች ግብጻዊው አህመድ ሀሰን ነው። ግብጽ እ.አ.አ በ2006 ባዘጋጀችው 25ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ኮትዲቯርን በመለያ ምት በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። በወቅቱ አራት ግቦችን ያስቆጠረው የፈርኦኖቹ አጥቂ አህመድ ሀሰን በውድድሩ ላይ ባሳየው ድንቅ ብቃት ኮከብ ተጫዋች በመባል ተመርጧል። እ.አ.አ በ2010 በአንጎላ አስተናጋጅነት በተካሄደው 27ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ግብጽ ጋናን በማሸነፍ ዋንጫውን ለሰባተኛ ጊዜ አንስታለች። አጥቂው አህመድ ሀሰን አሁንም የውድድሩ ኮብ ተጫዋች ሆኗል። በውድድሩ ላይ ሶስት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ወሳኝ አስተዋጽኦ አድርጓል። ከ34ቱ የአፍሪካ ዋንጫ የኮከብ ተጫዋቾች ሽልማት ውስጥ ግብጽ እና ካሜሮን በተመሳሳይ ሰባቱን በመውሰድ ቀዳሚውን ስፍራ ይዘዋል። መሐመድ ዲያብ አልታር (በቅጽል ስሙ አድ-ዲባ) ፣ አህመድ ሀሰን፣ ሀሰን ኤል-ሻዝሊ፣ መሐሙድ ኤል-ጎሃሪ እና ሆስኒ አብድ ራቦ ሽልማቱን ያገኙ የግብጽ ተጫዋቾች ናቸው። ሮጀር ሚላ፣ ሪጎበርት ሶንግ፣ ጂን-ፒየር ቶኮቶ፣ ቲኦፓል አቤጋ፣ ላውረን እና ክርስቲያን ባሶንግ የግል ክብሩን ማሸነፍ ችለዋል። የምዕራብ አፍሪካውያኑ ጋና እና ናይጄሪያ በተመሳሳይ አራት ተጨዋቾች የኮከብ ተጫዋችነት ሽልማቱን አግኝተዋል። አቢዲ ፔሌ፣ ኦሲ ኮፊ፣ ካሪም አብዱል ራዛቅ እና ክርስቲያን አትሱ ሽልማቱን የወሰዱ የጋና ተጫዋቾች ናቸው። ጄይ ጄይ ኢኮቻ፣ ራሺድ ያኪኒ፣ ክርስቲያን ቹኩ እና ዊሊያም ትሮስት-ኤኮንግ ከናይጄሪያ ሽልማቱን ወስደዋል። ከዛምቢያ ካሉሻ ቡዋሊያ እና ክሪስቶፈር ካቶንጎ፣ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ካዛዲ ምዋምባ እና ንዳዬ ሙላምባ እንዲሁም ራህባ ማጄር እና ኢስማኤል ቤናሰር ከአልጄሪያ ኮከብ ተጫዋች በመባል ተመርጠዋል። መንግስቱ ወርቁ (ኢትዮጵያ)፣ ቤኒ ማካርቲ (ደቡብ አፍሪካ)፣ ሳዲዮ ማኔ (ሴኔጋል)፣ ላውረን ፖኩ (ኮትዲቯር)፣ ፋውዚ አል-ኢሳዊ (ሊቢያ) እና ጆናታን ፒትሮፓ (ቡርኪናፋሶ) በተመሳሳይ አንድ አንድ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ ኮከብ ተጫዋች ሆነው መመረጥ ችለዋል። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች ማን ይሆናል? የሚለው ጉዳይ የእግር ኳስ አፍቃሪያንን ትኩረት የሳበ ጉዳይ ሆኗል።
ግብጽ በአፍሪካ ዋንጫ ጥሎ ማለፍ የገባች የመጀመሪያዋ ሀገር ሆናለች
Dec 26, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 17/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሁለት ተጠባቂ ጨዋታ ግብጽ ደቡብ አፍሪካን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በአጋዲር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ መሐመድ ሳላህ በ45ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። የግብጹ መሐመድ ሃኒ በመጀመሪያው አጋማሽ ማብቂያ ላይ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። በሁለተኛው አጋማሽ በ10 ተጫዋች የተጫወተችው ግብጽ ውጤቷን አስጠብቃ ወጥታለች። ደቡብ አፍሪካ በማራኪ ጨዋታ የታጀበ እንቅስቃሴ ብታደርግም የግብጽን ተከላካይ መስመር ሰብራ መግባት አልቻለችም። ውጤቱን ተከትሎ ግብጽ በስድስት ነጥብ አንድ ጨዋታ እየቀራት ወደ ጥሎ ማለፉ የገባች የመጀመሪያዋ ሀገር ሆናለች። ደቡብ አፍሪካ በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ምድብ ዛሬ በተደረገ ጨዋታ አንጎላ እና ዚምባቡዌ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ መድን ጋር አቻ ተለያየ
Dec 26, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 17/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት ሲዳማ ቡና እና ኢትዮጵያ መድን ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ረመዳን በ18ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ኢትዮጵያ መድን መሪ ሆኗል። ብርሃኑ በቀለ በ29ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ሲዳማ ቡናን አቻ አድርጋለች። የሲዳማ ቡናው አጥቂ ሀብታሙ ታደሰ ከእረፍት መልስ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ውጤቱን ተከትሎ የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ነጥቡን ወደ 22 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ፋሲል ከነማ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ለማስፋት ያገኘውን እድል አልተጠቀመም። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ13 ነጥብ ደረጃውን ከ16ኛ ወደ 13ኛ ከፍ አድርጓል። ዛሬ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ መቻል አዳማ ከተማን 3 ለ 1 አሸንፏል። መቻል ከስድስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ12ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከታህሳስ 20 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እንደሚካሄዱ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።