ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ኢትዮጵያ ቡና በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን አግኝቷል
Oct 23, 2025 39
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት የመጀመሪያ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ቡና አዲስ አዳጊውን ነጌሌ አርሲን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አቡበከር አዳሙ እና በፍቃዱ አለማየሁ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ገብረመስቀል ዱባለ ለነጌሌ አርሲ ብቸኛዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ቡናማዎቹ በሊጉ የመጀመሪያ ድላቸውን አሳክተዋል። በአንጻሩ ነጌሌ አርሲ በሊጉ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል
Oct 23, 2025 77
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 13/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት በመጀመሪያ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ኢትዮጵያ ቡና ከነገሌ አርሲ ጋር ከቀኑ 7 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቡናማዎቹ በመጀመሪያው ሳምንት በደርቢው ጨዋታ በቅዱስ ጊዮርጊስ 1 ለ 0 መሸነፋቸው የሚታወስ ነው። አዲስ አዳጊው ነገሌ አርሲ በሊጉ የመክፈቻ መርሃ ግብር ከአርባምንጭ ከተማ ጋር አንድ አቻ ተለያይቷል። ሁለቱ ክለቦች በሊጉ የመጀመሪያ ግንኙነታቸው ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይጫወታሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ሸገር ከተማ ከአዳማ ከተማ ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በመጀመሪያ ጨዋታ በኢትዮ ኤሌክትሪክ 1 ለ 0 የተሸነፈ ሲሆን አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ መድን ጋር ባደረገው ጨዋታ ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። በተያያዘም በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ሁለት ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከፋሲል ከነማ ይጫወታሉ። ወልዋሎ በመጀመሪያ ጨዋታው በሲዳማ ቡና የ4 ለ 1 ሽንፈት ያስተናገደ ሲሆን ፋሲል ከነማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር አንድ አቻ ወጥቷል። ሁለቱ ክለቦች በ2017 ዓ.ም የውድድር ዓመት በሊጉ ሁለት ጊዜ ተገናኝተው ፋሲል ከነማ ሁለቱንም ጨዋታዎች ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ወላይታ ድቻ ከድሬዳዋ ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በመጀመሪያው ሳምንት ወላይታ በመቻል 1 ለ 0፣ ድሬዳዋ ከተማ በሀዋሳ ከተማ የ2 ለ 0 ሽንፈት አስተናግደዋል። ቡድኖቹ በሊጉ የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ።
በሻምፒዮንስ ሊጉ ተጠባቂ ጨዋታ ሪያል ማድሪድ ጁቬንቱስን አሸነፈ
Oct 23, 2025 64
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መርሃ ግብር ሪያል ማድሪድ ጁቬንቱስን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሳንቲያጎ በርናባው ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ጁድ ቤሊንግሃም በ57ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ሪያል ማድሪድ በሻምፒዮንስ ሊጉ ሶስተኛ ድሉን በማስመዝገብ ነጥቡን ወደ ዘጠኝ ከፍ አድርጓል። ጁቬንቱስ በውድድሩ የመጀመሪያ ሽንፈቱን ያስተናገደ ሲሆን እስከ አሁን ያገኘው ሁለት ነጥብ ብቻ ነው። በሌሎች ጨዋታዎች ቼልሲ አያክስ አምስተርዳምን 5 ለ 1 አሸንፏል። ማርክ ጉዊ፣ ሞይሰስ ካይሴዶ እና ታይሪክ ጆርጅ በጨዋታ ኢንዞ ፈርናንዴዝ እና እስቴቫኦ ዊሊያን በፍጹም ቅጣት ምት ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ዉት ዌግሆረስት በፍጹም ቅጣት ምት ለአያክስ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ኬኔት ቴይለር በ15ኛው ደቂቃ ከአያክስ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ሊቨርፑል ወደ ጀርመን በማቅናት ባደረገው ጨዋታ ኢንትራክት ፍራንክፈርትን 5 ለ 1 አሸንፏል። ሁጎ ኢኪቲኬ፣ ቨርጂል ቫን ዳይክ፣ ኢብራሂማ ኮናቴ፣ ኮዲ ጋፕኮ እና ዶምኒክ ስቦዝላይ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ራስመስ ክሪስታይንሰን ለፍራንክፈርት ብቸኛውን ጎል ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ባየር ሙኒክ በሃሪ ኬን፣ ሉዊስ ዲያዝ፣ ኒኮላስ ጃክሰን እና ሌናርት ካርል ግቦች ክለብ ብሩዥን 4 ለ 0 ረቷል። ስፖርቲንግ ሊዝበን ማርሴይን 2 ለ 1 ሲያሸንፍ፣ ሞናኮ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ እና አትላንታ ከስላቪያ ፕራግ ያደረጓቸው ጨዋታዎች ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች አትሌቲኮ ቢልባኦ ካራባግን፣ ጋላታሳራይ ቦዶ ግሊምትን በተመሳሳይ 3 ለ 1 አሸንፈዋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ በታንዛንያ ተሸንፏል
Oct 22, 2025 127
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 12/2018 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን በ16ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ ከታንዛንያ አቻው ጋር ባደረገው የመጀመሪያ ጨዋታ የ2 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። በአዛም ኮምፕሌክስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አይሻ ጁማ እና ጃሚላ ራጃብ ለታንዛንያ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሉሲዎቹ የመልስ ጨዋታቸውን ጥቅምት 18 ቀን 2018 ዓ.ም ያደርጋሉ። የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ለአፍሪካ ዋንጫ ለመሳተፍ በመልሱ ጨዋታ ከሶስት እና ከዚያ በላይ ጎል በማስቆጠር ማሸነፍ ይጠበቅበታል።
የአውሮፓ ኃያላኑ ሪያል ማድሪድ እና ጁቬንቱስ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Oct 22, 2025 109
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 12/2018(ኢዜአ):- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዛሬ ዘጠኝ ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። በሳንቲያጎ በርናባው ስታዲየም ሪያል ማድሪድ ከጁቬንቱስ ምሽት 4 ሰዓት ላይ የሚያደርጉት ጨዋታ የተመልካቾችን ቀልብ ስቧል። የ15 ጊዜ የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ሪያል ማድሪድ በሊግ ውድድር ፎርማቱ በስድስት ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። የሁለት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ጁቬንቱስ በሁለት ነጥብ 24 ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ክለቦች በሻምፒዮንስ ሊጉ ሲገናኙ ለ22ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 21 የእርስ በእርስ ጨዋታዎች ሪያል ማድሪድ 10 ጨዋታዎችን ሲያሸንፍ ጁቬንቱስ ዘጠኝ ጊዜ ድል ቀንቶታል። ሁለት ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በጨዋታዎቹ ሪያል ማድሪድ 25፣ ጁቬንቱስ 26 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቡድኖቹ ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ የተገናኙት እ.አ.አ በ2017/18 በሩብ ፍጻሜ ሲሆን ሪያል ማድሪድ በድምር ውጤት 4 ለ 3 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ሪያል ማድሪድ በላሊጋው በ24 ነጥብ ሊጉን እየመራ የሚገኝ ሲሆን ጁቬንቱስ በሴሪአው በ12 ነጥብ 7ተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የቡድኖቹ የአውሮፓ መድረክ ፉክክር ከ60 ዓመት በላይ የዘለቀ ነው። የዛሬው ጨዋታም የዚሁ ተቀናቃኝነት ቀጣይ አካል ነው። የ45 ዓመቱ ስሎቬኒያዊ ስላቫኮ ቪንቺች የሁለቱ ቡድኖች ወሳኝ ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። ቼልሲ ከአያክስ፣ ኢንትራክት ፍራንክፈርት ከሊቨርፑል፣ ሞናኮ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ፣ ባየር ሙኒክ ከክለብ ብሩዥ፣ ስፖርቲንግ ሊዝበን ከማርሴይ እና አትላንታ ከስላቪያ ፕራግ በተመሳሳይ ከምሽቱ አራት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አትሌቲኮ ቢልባኦ ከካራባግ እና ጋላታሳራይ ከቦዶ ግሊምት በተመሳሳይ ከምሽቱ 1 ሰዓት ከ45 ላይ ይጫወታሉ።
ኢትዮጵያ በሴቶች እግር ኳስ የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ከታንዛንያ ጋር ዛሬ ጨዋታዋን ታደርጋለች
Oct 22, 2025 97
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 12/2018(ኢዜአ):- የኢትዮጵያ ሴቶች እግር ኳስ ብሄራዊ ቡድን በ16ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ የመጀመሪያ ጨዋታውን ከታንዛንያ አቻ ጋር ዛሬ ያከናውናል። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ከቀኑ 11 ሰዓት በአዛም ኮምፕሌክስ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ በመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ዩጋንዳን በደርሶ መልስ ውጤት በማሸነፍ ለመጨረሻው ዙር አልፋለች። ተጋጣሚዋ ታንዛንያ ኢኳቶሪያል ጊኒን በድምር ውጤት በማሸነፍ ወደ ወሳኙ ፍልሚያ ተሸጋግራለች። በአሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ የሚመራው የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ከታንዛንያ ጋር ላለበት ወሳኝ ጨዋታ ለአራት ሳምንታት ገደማ በአዲስ አበባ ዝግጅቱን አድርጓል። አሰልጣኝ ዮሴፍ ለጨዋታው ዝግጅት ሲያደርግ የነበረውን ስብስብ ወደ 21 በመቀነስ ወደ ታንዛንያ አምርቷል። ሮማን አምባዬ፣ ቤተልሄም መንተሎ፣ ፀጋ ንጉሤ፣ ቤዛዊት ንጉሤ እና ብዙዓየሁ ታደሰ (በጉዳት) ከስብስቡ የቀነሱ ተጫዋቾች መሆናቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል። ሉሲዎቹ ጥቅምት 10 ቀን 2018 ዓ.ም ዳሬሰላም የገቡ ሲሆን ለጨዋታው የመጨረሻ ልምምዳቸውን በአዛም ኮምፕሌክስ ስታዲየም አድርገዋል። በባካሪ ሺሜ የሚመራው የታንዛንያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ለጨዋታው በዳሬ ሰላም ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቷል። ኢትዮጵያ እና ታንዛንያ በውድድና የወዳጅነት ጨዋታዎች ላይ ሲገናኙ የአሁኑ ለስድስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው አምስት የእርስ በእርስ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ሁለት ጊዜ ስታሸንፍ ታንዛንያ አንድ ጊዜ ድል ቀንቷታል። ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። ኢትዮጵያ በጨዋታዎቹ ስድስት ግቦችን ስታስቆጥር ታንዛንያ ሰባት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ሁለቱ ቡድኖች ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን እ.አ.አ በ2012 በጣምራ ባዘጋጁት 10ኛው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ለመሳተፍ በመጨረሻው ዙር ማጣሪያ ተገናኝተው ኢትዮጵያ በድምር ውጤት በማሸነፍ ለውድድሩ ማለፏ አይዘነጋም። በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ ኢትዮጵያ 128ኛ፣ ታንዛንያ 131ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። ዩጋንዳዊቷ አይሻ ናሉሊ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ትመራለች። የሁለቱ ሀገራት የማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ጥቅምት 18 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይደረጋል። ኢትዮጵያ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈች በታሪኳ ለአራተኛ ጊዜ በሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ መሳተፏን ታረጋግጣለች። በውድድሩ ላይ ለመሳተፍ የሚደረጉ የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ ጨዋታዎች ከጥቅምት 12 እስከ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ባለው ጊዜ እንደሚካሄዱ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል። እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት በሚካሄደው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጇን ሀገር ጨምሮ 16 ሀገራት ይሳተፋሉ።
አርሰናል አትሌቲኮ ማድሪድን በሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል
Oct 21, 2025 188
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጠባቂ መርሃ ግብር አርሰናል አትሌቲኮ ማድሪድን 4 ለ 0 ረቷል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቪክቶር ዮኮሬሽ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ጋብርኤል ማጋሌስ እና ጋብርኤል ማርቲኔሊ ቀሪዎቹን ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። መድፈኞቹ ከእረፍት መልስ ያሳዩት ድንቅ የማጥቃት እንቅስቃሴ ጨዋታውን እንዲያሸንፉ አድርጓቸዋል። አርሰናል በሻምፒዮንስ ሊጉ ሶስተኛ ድሉን በማስመዝገብ ነጥቡን ወደ ዘጠኝ ከፍ አድርጓል። አትሌቲኮ ማድሪድ በውድድሩ ሁለተኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በሌሎች ጨዋታዎች የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ፒኤስጂ ባየር ሌቨርኩሰንን ከሜዳው ውጪ 7 ለ 2 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ዴዚሪ ዱዌ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኡስማን ዴምቤሌ፣ ክቪቻ ክቫራትሽኬሊያ፣ ቪቲኒያ፣ ዊሊያን ፓቾ እና ኑኖ ሜንዴዝ ቀሪዎቹን ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አሌክስ ጋርሺያ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ለሌቨርኩሰን ግቦቹን አስቆጥሯል። ሮበርት አንድሪች ከሌቨርኩሰን፣ ኢልያ ዛባርኒ ከፒኤስጂ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብተዋል። ፒኤስጂ በዘጠኝ ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ማንችስተር ሲቲ በአርሊንግ ሃላንድ እና በርናንዶ ሲልቫ ግቦች ቪያሪያልን 2 ለ 0 አሸንፏል። ኒውካስትል ዩናይትድ ቤኔፊካን 3 ለ 0 ረቷል። ሃርቪ ባርንስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አንቶኒ ጎርደን ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ፒኤስቪ ኤይንድሆቨን ናፖሊን 6 ለ 2፣ ኢንተር ሚላን ዩኒየን ሴይንት ዢሎሽን 4 ለ 0 እና ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ኮፐንሃገንን 4 ለ 2 አሸንፈዋል።
ባርሴሎና ኦሎምፒያኮስን በሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል
Oct 21, 2025 128
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 11/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መርሃ ግብር ባርሴሎና ኦሎምፒያኮስን 6 ለ 1 ረቷል። ማምሻውን በሉዊስ ካምፓኒስ ኦሊምፒክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፌርሚን ሎፔዝ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ማርከስ ራሽፎርድ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ላሚን ያማል በፍጹም ቅጣት ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። አዩብ ኤልካቢ በፍጹም ቅጣት ምት ለኦሎምፒያኮስ ብቸኛዋን ጎል አስቆጥሯል። የኦሎምፒያኮሱ ሳንቲያጎ ሄዜ በሁለት ቢጫ ካርድ በ57ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ተጫዋቹ ሁለተኛ ቢጫ ያየበት ጥፋት አወዛጋቢ ነበር። የሄዜ መውጣት በቀሪው የጨዋታ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ልዩነት ፈጥሯል። በተመሳሳይ ሰዓት በተደረገ ጨዋታ ካይራት አልማቲ እና ፓፎስ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል። የፓፎሱ ጆአኦ ኮሬያ በአራተኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል።
በሻምፒዮንስ ሊጉ የአርሰናል እና አትሌቲኮ ማድሪድ ጨዋታ ይጠበቃል
Oct 21, 2025 149
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 11/2018 (ኢዜአ):- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሶስተኛ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ። አርሰናል እና አትሌቲኮ ማድሪድ ምሽት 4 ሰዓት ላይ በኤምሬትስ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ የተመልካቾች ትኩረት አርፎበታል። ሁለቱ ክለቦች በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ቡድኖቹ ከዚህ ቀደም በአውሮፓ መድረክ የተገናኙት እ.አ.አ በ2017/18 በዩሮፓ ሊግ ግማሽ ፍጻሜ ነበር። በወቅቱ በኤምሬትስ በተካሄደው ጨዋታ አንድ አንድ አቻ ተለያይተው በመልሱ ጨዋታ አትሌቲኮ በሜዳው 1 ለ 0 በማሸነፍ በድምር ውጤት ለፍጻሜ አልፏል። የማድሪዱ ክለብ በፍጻሜው ማርሴይን በማሸነፍ ዋንጫውን ማንሳቱ አይዘነጋም። በሊግ ምዕራፍ የደረጃ ሰንጠረዥ አርሰናል በስድስት ነጥብ፤ አትሌቲኮ ማድሪድ በሶስት ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። አርሰናል በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ በ19 ነጥብ እየመራ ሲሆን አትሌቲኮ ማድሪድ አትሌቲኮ ማድሪድ በ16 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ44 ዓመቱ ጣልያናዊ ዳቪዴ ማሳ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች በቤይ አሬና ባየር ሌቨርኩሰን የወቅቱን የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂን ምሽት 4 ሰዓት ላይ ያስተናግዳል። ቪያሪያል ከማንችስተር ሲቲ፣ ኮፐንሃገን ከቦሩሲያ ዶርትሙንድ፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ከቤኔፊካ፣ ፒኤስቪ አይንድሆቨን ከናፖሊ እና ዩኒየን ሴይንት ጊሎይስ ከኢንተር ሚላን በተመሳሳይ ምሽት 4 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባርሴሎና ከኦሎምፒያኮስ እና ካይራት አልማቲ ከፓፎስ በተመሳሳይ ምሽት 1 ሰዓት ከ45 ላይ የሚካሄዱ ጨዋታዎች ናቸው።
ባህር ዳር ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ድል ቀንቷቸዋል
Oct 20, 2025 144
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 10 /2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ተጋጣሚዎቻቸውን በማሸንፍ ዓመቱን በድል ጀምረዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ ባህር ዳር ከተማ ሀድያ ሆሳዕናን 3 ለ 1 አሸንፏል። ክንዱ ባየልኝ፣ አማኑኤል ገብረሚካኤል እና ሳቲ ኦሴ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጫላ ተሺታ ለሀድያ ሆሳዕና ብቸኛዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የሀድያ ሆሳዕናው ኤልያስ መሐመድ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ጨዋታ ምድረ ገነት ሽሬ በዳንኤል ዳርጌ ግብ መቀሌ 70 እንደርታን 1 ለ 0 አሸንፏል። አስቀድሞ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን ከአዳማ ከተማ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ውጤቶቹን ተከትሎ የአንደኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የሁለተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከጥቅምት 13 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳሉ።
ኢትዮጵያ መድን እና አዳማ ከተማ ነጥብ ተጋርተዋል
Oct 20, 2025 109
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 10 /2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሃ ግብር ኢትዮጵያ መድን እና አዳማ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ዛሬ ከቀትር በኋላ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአዳማ ከተማው ሃይደር ሸረፋ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ሃይደር አምና በአምበልነት ኢትዮጵያ መድንን እየመራ የሊጉን ዋንጫ ማንሳቱ የሚታወስ ሲሆን ኮከብ ተጫዋች ሆኖ ተመርጦም ነበር። ኢትዮጵያ መድን የዋንጫ ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን ነጥብ በመጣል ጀምሯል። በሌሎች የአንደኛ ሳምንት መርሃ ግብሮች ባህር ዳር ከተማ ከሀድያ ሆሳዕና በአዲስ አበባ ስታዲየም፣ ምድረ ገነት ሽሬ ከመቀሌ 70 እንደርታ ጋር በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተመሳሳይ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ኢትዮጵያ መድን የዋንጫ ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን ከአዳማ ከተማ ጋር በሚያደርገው ጨዋታ ይጀምራል
Oct 20, 2025 116
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 10 /2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከነዚህ መርሃ ግብሮች መካከል አዳማ ከተማ እና ኢትዮጵያ መድን ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ የሚያደርጉት ጨዋታ ይገኝበታል። ኢትዮጵያ መድን በ2017 ዓ.ም የውድድር ዓመት በ73 ነጥብ የሊጉን ዋንጫ ለመጀመሪያ ጊዜ ማንሳቱ ይታወቃል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ አምና በሊጉ በ39 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። መድን የዋንጫ ክብሩን አስጠብቆ ለመቆየት የሚያደርገውን ጉዞ ዛሬ ይጀምራል። በአንጻሩ አዳማ ከተማ ባለፈው የውድድር ዓመት ከነበረው ደካማ አቋም የተሻለ እንቅስቃሴ ለማድረግ ይጫወታል። ቡድኖቹ በ2017 ዓ.ም በሊጉ ሁለት ጊዜ ተገናኝተው ኢትዮጵያ መድን ሁለቱንም ጨዋታዎች ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከሀድያ ሆሳዕና ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረገነት ሽሬ ከመቀሌ 70 እንደርታ ከቀኑ 10 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታል።
መቻል የውድድር ዓመቱን በድል ጀምሯል
Oct 19, 2025 151
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት ጨዋታ መቻል ወላይታ ድቻን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ መናፍ ኢሞሮ በ92ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል በማስቆጠር ለቡድኑ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አስገኝቷል። ዛሬ በፕሪሚየር ሊጉ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 በማሸነፍ የደርቢ ድል ተቀዳጅቷል። ፋሲል ከነማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል።
በተጠባቂው የሊግ ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ ሊቨርፑልን አሸነፈ
Oct 19, 2025 119
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የስምንተኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሃ ግብር ማንችስተር ዩናይትድ ሊቨርፑልን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ብሪያን ምቡዌሞ እና ሃሪ ማጓየር የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኮዲ ጋፕኮ ለሊቨርፑል ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ በሊጉ ሶስተኛ ተከታታይ ሽንፈቱን ያስተናገደው የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ሊቨርፑል በ15 ነጥብ ከሁለተኛ ወደ አራተኛ ዝቅ ብሏል። ከሊጉ አርሰናል ጋር ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ከፍ ብሏል። ማንችስተር ዩናይትድ በ13 ነጥብ ደረጃውን ከ11ኛ ወደ 9ኛ ከፍ አድርጓል። ዩናይትድ በሩበን አሞሪም ስር በሊጉ ተከታታይ ድሉን ለመጀመሪያ ጊዜ አስመዝግቧል። ቀን ላይ በተደረገ ሌላኛው ጨዋታ አስቶንቪላ ቶተንሃም ሆትስፐርስን 2 ለ 1 አሸንፏል።
በደርቢው ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ኢትዮጵያ ቡናን አሸነፈ
Oct 19, 2025 123
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት ተጠባቂ መርሃ ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስ ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አጥቂው አቤል ያለው በ66ኛው ደቂቃ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ጋናዊው የኢትዮጵያ ቡና ግብ ጠባቂ ኢብራሂም ዳንላድ በአቤል ያለው ላይ በሰራው ጥፋት በ53ኛው ደቂቃ ላይ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ኢትዮጵያ ቡና የተወሰደበት የቁጥር ብልጫ በጨዋታው ላይ ልዩነት የፈጠረበት አጋጣሚ ነበር። በሁለቱ ቡድኖች የ51ኛው የሊግ የደርቢ ጨዋታ በቅዱስ ጊዮርጊስ አሸናፊነት ተጠናቋል። ከ17 ሺህ በላይ ደጋፊ በስታዲየም በመገኘት የተከታተለውን ጨዋታ ደጋፊው ድምቀት ሰጥቶታል። በተመሳሳይ ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፋሲል ከነማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በረከት ግዛው ለፋሲል ከነማ፣ ዘላለም አባተ ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ መቻል ከወላይታ ድቻ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የታሪካዊ ባላንጣዎቹ ፍልሚያ በአንፊልድ ሮድ
Oct 19, 2025 130
አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የስምንተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሊቨርፑል እና ማንችስተር ዩናይትድ ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 12 ሰዓት ከ30 በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ይካሄዳል። ሊቨርፑል በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው ሰባት ጨዋታዎች 5 ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። ቡድኑ በጨዋታዎቹ 13 ግቦችን ሲያስቆጥር 9 ግቦችን አስተናግዷል። ቀያዮቹ በ15 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ተጋጣሚው ማንችስተር ዩናይትድ በበኩሉ በሊጉ ባካሄዳቸው 7 ጨዋታዎች 3 ጊዜ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ 3 ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ ነጥብ ተጋርቷል። ቡድኑ በጨዋታዎቹ 9 ግቦችን ሲያስቆጥር 11 ጎሎች ተቆጥረውበት በ10 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች እስከ አሁን በሁሉም ውድድሮች 219 ጊዜ ተገናኝተው ማንችስተር ዩናይትድ 85 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ሲይዝ ሊቨርፑል 73 ጊዜ በማሸነፍ 61 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። ሁለቱ ክለቦች በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ባደረጓቸው 62 ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ 28 ጊዜ ሲያሸንፍ ሊቨርፑል 19 ጊዜ አሸንፎ 15 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በአንጻሩ ማንችስተር ዩናይትድ በውጤት ማጣት ቀውስ ውስጥ ሲሆን በፕሪሚየር ሊጉ ባለፉት ሶስት ተከታታይ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ለ131 ዓመታት የዘለቀ ታሪካዊ ተቀናቃኝነት ያላቸው ሁለቱ ክለቦች በተመሳሳይ የሊጉን ዋንጫ 20 ጊዜ በማንሳት ስኬታማ ክለቦች ናቸው። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል የዛሬው ጨዋታ ከሁለት ተከታታይ የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርገው ፍልሚያ ነው። ቡድኑ ካሸነፈ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አንድ ዝቅ ያደርጋል። ተጋጣሚው ማንችስተር ዩናይትድ ካሸነፈ በሩበን አሞሪም ስር በሊጉ ለመጀመሪያ ጊዜ ተከታታይ ድል ያስመዘግባል። የ40 ዓመቱ እንግሊዛዊ ማይክል ኦሊቫር ወሳኙን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌላኛው የሊጉ መርሃ ግብር ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከአስቶንቪላ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ 51ኛው የፕሪሚየር ሊግ የደርቢ ጨዋታ ዛሬ ይጠበቃል
Oct 19, 2025 121
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 9/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ቡና እና ቅዱስ ጊዮርጊስ የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ የእግር ኳስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል። ቡድኖቹ በሊጉ እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ ለ51ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም 50 ጊዜ ተጫውተው ቅዱስ ጊዮርጊስ 21 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ሲይዝ ኢትዮጵያ ቡና 9 ጊዜ ድል ቀንቶታል። 20 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በ50ዎቹ ጨዋታዎች በድምሩ 97 ጎሎች የተቆጠሩ ሲሆን ቅዱስ ጊዮርጊስ 63 እንዲሁም ኢትዮጵያ ቡና ደግሞ 34 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሁለቱ ክለቦች በ2017 ዓ.ም የውድድር ዓመት ባደረጓቸው ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ በቀሪው ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። በ2017 ዓ.ም ኢትዮጵያ ቡና በ60 ነጥብ ሁለተኛ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ49 ነጥብ 9ኛ ደረጃን ይዘው ማጠናቀቃቸው የሚታወስ ነው። ኢትዮጵያ ቡና የሊጉን ዋንጫ አንድ ጊዜ ያነሳ ሲሆን ቅዱስ ጊዮርጊስ 16 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። የሁለቱ ክለቦች በርካታ ደጋፊዎች ለጨዋታው ድምቀት ይሰጡታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ፋሲል ከነማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከቀኑ 9 ሰዓት፣ መቻል ከወላይታ ድቻ ከምሽቱ 12 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በደርቢው ጨዋታ ባየር ሙኒክ ቦሩሲያ ዶርትሙንድን አሸነፈ
Oct 18, 2025 114
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በጀርመን ቡንድስሊጋ የሰባተኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሃ ግብር ባየር ሙኒክ ቦሩሲያ ዶርትሙንድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሃሪ ኬን እና ማይክል ኦሊሴ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጁሊያን ብራንድ ለዶርትሙንድ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ባየር ሙኒክ በ21 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። በሊጉ የመጀመሪያ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቦሩሲያ ዶርትሙንድ በ14 ነጥብ ከነበረበት ሁለተኛ ደረጃ ወደ አራተኛ ዝቅ ብሏል።
አርሰናል የሊጉን መሪነት ዳግም ተረከበ
Oct 18, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የስምንተኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርሰናል ፉልሃምን 1 ለ 0 ተሸንፏል። ማምሻውን በክራቫን ኮቴጅ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሊያንድሮ ትሮሳርድ በ58ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ አሳርፏል። አርሰናል በሊጉ ከማዕዘን ምት ያስቆጠራቸው የግቦች ብዛት ሰባት አድርሷል። በሊጉ ስድስተኛ ድሉን ያስመዘገበው አርሰናል በ19 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከማንችስተር ሲቲ ተረክቧል። በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ፉልሃም በስምንት ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል።
በፕሪሚየር ሊጉ ስምንተኛ ሳምንት ማንችስተር ሲቲ ኤቨርተንን አሸነፈ
Oct 18, 2025 96
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ስምንተኛ ሳምንት ማንችስተር ሲቲ ኤቨርተንን 2 ለ 0 አሸንፏል። በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሊንግ ሃላንድ ሁለቱን ግቦች አስቆጥሯል። ሃላንድ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ 11 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን አጠናክሯል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ በ16 ነጥብ ደረጃውን በጊዚያዊነት ወደ አንደኛ ከፍ አድርጓል። በርንሌይ ሊድስ ዩናይትድን፣ ሰንደርላንድ ዎልቭስን በተመሳሳይ 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ብራይተን ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 1 ረቷል። ቦርንማውዝ ከክሪስታል ፓላስ ሶስት አቻ ተለያይተዋል። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ፉልሃም ከአርሰናል በክራቫን ኮቴጅ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።