ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ ሚያዚያ 16 ወደ ውድድር ይመለሳል
Apr 6, 2026 131
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 28/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሚያዚያ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ዳግም ወደ ውድድር እንደሚመለስ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታወቀ። ፕሪሚየር ሊጉ በኢትዮጵያ ከ17 እና ከ18 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድኖች የውድድር ተሳትፎ ምክንያት መቋረጡ ይታወቃል። ከ21ኛው ሳምንት በኋላ የተቋረጠው ፕሪምየር ሊጉ ከሚያዚያ 16 ጀምሮ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም እንደሚቀጥል ፌዴሬሽኑ አመልክቷል።
ዓለም አቀፍ የአንድ ቀን የአትሌቲክስ ውድድር በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል
Apr 6, 2026 143
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 28/2018 (ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፍ የአንድ ቀን የአትሌቲክስ ውድድር (One day meeting ) ሚያዝያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስታዲየም እንደሚካሄድ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ። የአዲስ አበባ ስታዲየም መሮጫ ትራክ እድሳት ተጠናቆ አገልግሎት ለመስጠት ዝግጁ መሆኑንም አመልክቷል። ይህን ተከትሎም ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የምታስተናግደው ዓለም አቀፍ የአንድ ቀን የአትሌቲክስ ውድድር (One Day Meeting) በአዲስ አበባ ስቴዲየም እንደሚካሄድ ሚኒስቴሩ አረጋግጧል። ውድድሩ ከተለያዩ ሀገሮች የተውጣጡ አትሌቶች የሚሳተፉበት ሲሆን፤ አሸናፊ ለሚሆኑ አትሌቶች ከፍተኛ ሽልማት ያገኛሉ። የአንድ ቀን ውድድሩ የዓለም አትሌቲክስ ዓመታዊ የኢንተርኮንቲነንታል ውድድር አካል ነው።
በኤፍኤ ካፕ ግማሽ ፍጻሜ ማንችስተር ሲቲ ከሳውዝሃምፕተን ቼልሲ ከሊድስ ዩናይትድ ይጫወታሉ
Apr 5, 2026 379
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፦ የኤፍኤ ካፕ የግማሽ ፍጻሜ የዕጣ ማውጣት ስነ ስርዓት ማምሻውን በዌስትሃም ዩናይትድ ለንደን ስታዲየም ተደርጓል። በዚሁ መሰረት ማንችስተር ሲቲ ከሳውዝሃምፕተን እና ቼልሲ ከሊድስ ዩናይትድ በግማሽ ፍጻሜው ይገናኛሉ። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ሚያዚያ 17 እና 18 ቀን 2018 ዓ.ም በዌምብሌይ ስታዲየም ይካሄዳሉ። 154 ዓመታትን ያስቆጠረው ኤፍኤ ካፕ የዓለማችን አንጋፋው የእግር ኳስ ውድድር ነው።
ሊድስ ዩናይትድ ከ39 ዓመታት በኋላ ለኤፍኤ ካፕ ግማሽ ፍጻሜ አለፈ
Apr 5, 2026 231
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኤፍኤ ካፕ የመጨረሻ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ ሊድስ ዩናይትድ ዌስትሃም ዩናይትድን በመለያ ምት አሸንፏል። ማምሻውን በለንደን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አዎ ታናካ በ26ኛው ደቂቃ በጨዋታ እና ዶምኒክ ካልቨርት-ልዊን በ75ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ያስቆጠሯቸው ግቦች ሊድስ ዩናይትድን መሪ አድርጓል። ጨዋታው በሊድስ ዩናይትድ አሸናፊነት ተጠናቀቀ ሲባል ማቴውስ ፈርናንዴዝ በ93ኛው እና አክሴል ዲሳሲ በ96ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፏቸው ጎሎች ዌስትሃም ዩናይትድ አቻ ሆኗል። ጨዋታው በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሁለት አቻ በመጠናቀቁ 30 ደቂቃ ተጨምሯል። በጭማሪ ሰዓት አሸናፊው ባለመለየቱ ምክንያት ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቷል። በዚሁ መሰረት ሊድስ ዩናይትድ 4 ለ 2 በማሸነፍ ከ39 ዓመታት በኋላ ለኤፍኤ ካፕ ግማሽ ፍጻሜ አልፏል። ዌስትሃም ዩናይትድ ዩናይትድ ከ35 ዓመታት በኋላ ወደ ግማሽ ፍጻሜ የማለፍ ህልሙ አልተሳካም። ጨዋታውን ተከትሎ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ተጠናቋል። ማንችስተር ሲቲ፣ ቼልሲ፣ ዌስትሃም ዩናይትድ እና ሳውዝሃምፕተን ለግማሽ ፍጻሜ ያለፉ ክለቦች ናቸው።
ሐዋሳ ከተማ እና ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ነጥብ ተጋሩ
Apr 5, 2026 279
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፡- በ2018 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት የተገናኙት ሀዋሳ ከተማ እና ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ 2 አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው የተካሄደው 10 ሠዓት ላይ በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ነው። በዚሁ ጨዋታም ያሬድ ብሩክ እና ሽመልስ በቀለ ለሐዋሳ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። እንዲሁም ነጻነት ገ/መድኅን እና ዳዊት ገብሩ ለወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ግቦቹን ከመረብ አሳርፈዋል። ቀደም ብሎ 9 ሠዓት ላይ በተካሄደ ጨዋታ ነጌሌ አርሲ አዳማ ከተማን 2 ለ 1 ረትቷል።
ነጌሌ አርሲ አዳማ ከተማን አሸንፏል
Apr 5, 2026 142
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፡- በ2018 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ነጌሌ አርሲ አዳማ ከተማን 2 ለ 1 ረትቷል። 9 ሠዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ፤ ሁለቱም እስከ እረፍት ድረስ ያለምንም ግብ አቻ ሆነው ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል። ከእረፍት መልስ ዳዊት ተፈራ እና ሮሆቦት ሰላሎ ለነጌሌ አርሲ እንዲሁም ዳዋ ሁቴሳ ለአዳማ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎም ነጌሌ አርሲ በ41 ነጥብ 3ኛ እንዲሁም አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ 8ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ።
ውድድሩ ህብረ ብሄራዊ አንድነትና ሀገራዊ መስተጋብርን በአንድ መድረክ ያሳየ ነው
Apr 5, 2026 109
ሐረር፤መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የባህልና ስፖርቶች ውድድር ህብረ ብሄራዊ አንድነትና ሀገራዊ መስተጋብርን በአንድ መድረክ ያሳየ መሆኑን የኢትዮጵያ ባህል ስፖርቶች ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ወይዘሮ ህይወት መሀመድ ገለጹ፡፡ "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ'' በሚል መሪ ቃል ከመጋቢት 20 እስከ 27 በሐረሪ ክልል ሲካሄድ የነበረው 23ኛው የኢትዮጵያ የባህልና ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ፌስቲቫል ተጠናቋል። በውድድሩም በባህል ስፖርት ውድድር የኦሮሚያ ክልል አጠቃላይ አሸናፊ ሲሆን አማራ ክልልና አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር 2ኛ እና 3ኛ ሆነዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በባህል ፌስቲቫል በቀዳሚነት ሲያጠናቅቅ ኦሮሚያና ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች 2ኛ እና 3ኛ ሆነዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በበኩሉ የስፖርታዊ ጨዋነት ዋንጫ ተሸላሚ መሆን ችሏል። በመርሃ ግብሩ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርቶች ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ወይዘሮ ህይወት መሀመድ፡ የዘንድሮው የኢትዮጵያ የባህልና ስፖርቶች ውድድር ህብረ ብሄራዊ አንድነትና ሀገራዊ መስተጋብርን በአንድ መድረክ ያሳየ መሆኑን ገልጸዋል። የሐረሪ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙራድ አብዲ በበኩላቸው፤ በክልሉ የባህል ስፖርት እና ፌስታቫል መዘጋጀቱ መነቃቃትን ፈጥሯል ብለዋል። መርሃ ግብሩ ከስፖርት መድረክነት ባለፈ የህዝቦች ትስስርን በማጠናከርና መሠረተ ልማቶችን ማስተዋወቅ ያስቻለ መሆኑንም ገልጸዋል። አሸናፊ የነበሩ ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች ከእለቱ የክብር እንግዳና በብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጌቱ ወዬሳና የኢትዮጵያ ባህል ስፖርቶች ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት ወይዘሮ ህይወት መሀመድ እጅ የተዘጋጀላቸውን የዋንጫ ሽልማት ተረክበዋል። 24ኛውን የባህል ስፖርቶች ውድድር እና የባህል ስፖርት ፌስቲቫልን የሲዳማ ክልል እንዲያሰናዳ መመረጡም ይፋ ተደርጓል።
በተጠባቂው መርሐ ግብር ባርሴሎና አትሌቲኮ ማድሪድን በመርታት በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል
Apr 4, 2026 398
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በስፔን ላሊጋ የ30ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታ ባርሴሎና አትሌቲኮ ማድሪድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በዋንዳ ሜትሮፖሊታኖ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጁሊያኖ ሲሞኒ በ39ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል መሪ መሆን ችሏል። ማርከስ ራሽፎርድ በ42ኛው ደቂቃ ባሳረፈው ግብ ባርሴሎና አቻ ሆኗል። ተቀይሮ የገባው ሮበርት ሌዋንዶውስኪ በ87ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል ለባርሴሎና ወሳኝ ሶስት ነጥብ አስገኝቷል። የአትሌቲኮ ማድሪዱ ኒኮላስ ጎንዛሌዝ በመጀመሪያው አጋማሽ ማብቂያ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። የባርሴሎናው ጄራርድ ማርቲን ሁለተኛው አጋማሽ በተጀመረ 46ኛው ደቂቃ ቀይ ካርድ ቢመለከትም በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት ታይቶ የመጀመሪያ ውሳኔ ተሽሮ ወደ ቢጫ ካርድ ተቀይሯል። የቀይ ካርዱ መሻር የአትሌቲኮ ማድሪድ የቡድን አባላት እና ደጋፊዎችን ያስቆጣ ሲሆን ማርቲን በሰራው ጥፋት በቀይ ካርድ ሜዳ መውጣት ነበረበት በሚል ቅሬታቸውን አሰምተዋል። ባርሴሎና ያገኘውን የቁጥር ብልጫ ተጠቅሞ በፈጠረው ጫና ግብ አስቆጥሯል። ጨዋታው ጉልበት የተቀላቀለበት መሆኑ በርካታ ቢጫ ካርዶች እንዲመዘዙ አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ ባርሴሎና ነጥቡን ወደ 76 ከፍ በማድረግ መሪነቱን አጠናክሯል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። ከተከታዩ ሪያል ማድሪድ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሰባት ከፍ አድርጓል። ባርሴሎና በሊጉ 25ኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በሊጉ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አትሌቲኮ ማድሪድ በ57 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ሪያል ማድሪድ ዛሬ ባደረገው ጨዋታ በሪያል ማዮርካ ባልተጠበቀ ሁኔታ የ2 ለ 1 ሽንፈት አስተናግዷል። ባርሴሎና እና አትሌቲኮ ማድሪድ ረቡዕ መጋቢት 30 ቀን 2018 ዓ.ም በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሚያደርጉት የሩብ ፍጻሜ የመጀመሪያ ጨዋታ ይጠበቃል።
አርሰናል ከኤፍኤ ካፕ ውድድር ውጪ ሆነ
Apr 4, 2026 254
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በኤፍኤ ካፕ ሶስተኛ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ ሳውዝሃምፕተን አርሰናልን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በሴንት ሜሪ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሮስ ስቲዋርት እና ሼ ቻርልስ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ቻርልስ በ85ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል ሳውዝሃምፕተን አሸናፊ አድርጓል። ለአርሰናል ቪክቶር ዮኮሬስ ብቸኛውን ግብ አስቆጥሯል። በጨዋታው አርሰናል ብልጫ ወስዶ ቢጫወትም ተጨማሪ ጎል ማስቆጠር አልቻለም። ተጋጣሚው ሳውዝሃምፕተን ያገኛቸውን የግብ እድሎች በሚገባ ተጠቅሟል። ውጤቱን ተከትሎ 14 ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት ስኬታማ የሆነው አርሰናል በሩብ ፍጻሜው ተሰናብቷል። ለአራት ዋንጫዎች ሲፎካከር የነበረው አርሰናል የሚፎካከርባቸው ዋንጫዎች ብዛት ወደ ሁለት ዝቅ ብለዋል። በእንግሊዝ ሁለተኛ ዲቪዚዮን (ሻምፒዮንሺፕ) የሚገኘው ሳውዝሃምፕተን ሳይጠበቅ ወደ ግማሽ ፍጻሜ አልፏል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ማንችስተር ሲቲ ሊቨርፑልን 4 ለ 0፣ ቼልሲ ፖርት ቫሌን 7 ለ 0 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል።
ቼልሲ ፖርት ቫሌ ላይ ሰባት ግቦች አስቆጥሮ በማሸነፍ ወደ ግማሽ ፍጻሜው ተሻገረ
Apr 4, 2026 354
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በኤፍኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ቼልሲ ፖርት ቫሌን 7 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆሬል ሃቶ፣ ጆአኦ ፔድሮ፣ ቶሲን አዳራቢዮ፣ አንድሬይ ሳንቶስ፣ እስቴቫኦ ዊሊያን፣ አሌሃንድሮ ጋርናቾ እና የፖርት ቫሌው ጆርዳን ላውረንስ-ጋብርኤል በራሱ ላይ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጋርናቾ ግቧን ያስቆጠረው በፍጹም ቅጣት ምት ነው። በጨዋታው ላይ ቼልሲ ከፍተኛ ብልጫ ወስዷል። የስምንት ጊዜ የኤፍኤ ካፕ አሸናፊው ቼልሲ ለግማሽ ፍጻሜ ያለፈ ሁለተኛው ክለብ ሆኗል። በእንግሊዝ ሊግ ሶስተኛ እርከን ( ሊግ ዋን) የሚገኘው ፖርት ቫሌ ጉዞ ከሩብ ፍጻሜው ሊሻገር አልቻለም።
ሲዳማ ቡና በመሪነት ግስጋሴው ቀጥሏል
Apr 4, 2026 118
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና መቀሌ 70 እንደርታን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አቤል ያለው በ25ኛ ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ሲዳማ ቡና ነጥቡን ወደ 48 ከፍ በማድረግ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ ሃዋሳ ከተማ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ስምንት ከፍ ማድረግ ችሏል። ቡድኑ በአጠቃላይ በውድድር ዓመቱ ያሸነፋቸው ጨዋታዎች ብዛት 13 ደርሰዋል። በአንጻሩ በሊጉ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው መቀሌ 70 እንደርታ በ23 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው በሊጉ ከመረብ ላይ ያሳረፋቸውን ጎሎች ብዛት ወደ 11 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ25ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ሀዲያ ሆሳዕናን 2 ለ 1፣ ኢትዮጵያ ቡና ኢትዮጵያ መድንን 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ወላይታ ድቻ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
አዲስ ስፖርት ፓርክ የጀግኖች መዘከሪያ እና የትውልድ መገንቢያ ስጦታ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 4, 2026 424
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ አዲስ ስፖርት ፓርክ የጀግኖቻችን ክብር ህያው የሚሆንበት፣ የነገዋን ኢትዮጵያ በጤናማ ትውልድ የምንገነባበት ታላቅ ስጦታ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። በኢትዮጵያ የስፖርት ታሪክ አዲስ ምዕራፍ የከፈተውና በዓለም መድረክ ለሀገራቸው የወርቅ ሜዳሊያ ላስገኙ ጀግኖች አትሌቶች መታሰቢያ እንዲሆን ተደርጎ የተገነባው አዲስ ስፖርት ፓርክ ዛሬ ተመርቋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ፣ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው እና ጥሪ የተደረገላቸው ጀግኖች አትሌቶች በተገኙበት ፓርኩ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ባስተላለፉት መልዕክት በከተማዋ እምብርት በ5 ነጥብ 7 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈው ይህ ማዕከል፣ ሁሉንም ዓይነት የስፖርት ዘርፎች ያካተተ ነው ብለዋል። ፓርኩ የነገዋን ኢትዮጵያ በአካልና በሞራል የታነጸ ጤናማ ትውልድ ለመገንባት ታሳቢ ተደርጎ የተሰራ መሆኑን ገልጸው፤ ለጀግኖች አትሌቶች የክብር መግለጫ፣ ለወጣቶች የተስፋ ምንጭ፣ ለልጆች ደግሞ የደስታ ስጦታ ሆኖ መቅረቡን አመልክተዋል። የፓርኩ ልዩ ገጽታ በኦሎምፒክ መድረክ የወርቅ ሜዳሊያ በማምጣት የኢትዮጵያን ስም ላስጠሩ 15 የምንግዜም እንቁ አትሌቶች ለእያንዳንዳቸው የቆመው የክብር ሐውልት እንደሆነም አንስተዋል። ይህም ጀግኖችን በቁም ለማመስገንና ለተተኪው ታዳጊ ትውልድ እኔም እችላለሁ የሚል ትልቅ የስነ-ልቦና ተነሳሽነት ለመፍጠር ታስቦ የተከናወነ መሆኑን ነው ከንቲባዋ የገለጹት። ፓርኩ ለሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በሚመጥን መልኩ የተገነባ ሲሆን፣ ለባለሙያዎችና ለወጣቶች የኦሎምፒክ ደረጃቸውን የጠበቁ የመዋኛ ገንዳዎች፣ የእግር ኳስ፣ የቅርጫት ኳስ፣ የእጅ ኳስና የሜዳ ቴኒስ ሜዳዎችን መያዙን ጠቁመዋል። በተጨማሪም ስፖርትን የዘወትር የሕይወት ዘይቤ ለማድረግ የሚያግዙ ዘመናዊ የቤት ውስጥና የውጪ ጂም፣ የዌልነስ ሴንተር (Wellness Center) እና የ800 ሜትር የመሮጫ ትራክ ተካትተውበታል። ለልጆችና ለታዳጊዎች ደግሞ እንደ እድሜያቸው የተዘጋጁ ዘመናዊና ባህላዊ የመጫወቻ ስፍራዎች፣ የመዋኛ ገንዳዎችና የአሸዋ ላይ ስፖርት ሜዳዎች ተገንብተዋል። መሠረተ ልማቶቹ ህጻናት በአካልና በአዕምሮ እንዲያድጉ ታሳቢ ያደረጉ መሆናቸውን ከንቲባዋ በመልዕክታቸው ላይ ገልጸዋል። ይህ የልማት ፕሮጀክት ከስፖርት ባለፈ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስርን ያጠናክራል ያሉት ከንቲባዋ በተለይም ለካዛንችስ አካባቢ የልማት ተነሺዎች የተገነቡ የሴራሚክ መሸጫ ሱቆች፣ የዜጎችን ኑሮና ስራ ከልማቱ ጋር ለማስተሳሰር ያለውን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ተናግረዋል። በተጨማሪም 300 መኪናዎችን የሚይዝ ባለ ሁለት ቤዝመንት የመኪና ማቆሚያ፣ የአውቶቡስ ተርሚናል፣ እስከ 3 ሺህ ሰዎችን የሚያስተናግድ ሰፊ ፕላዛ እና ምቹ ሬስቶራንቶች ፓርኩን ለቤተሰብና ለጎብኚዎች ተመራጭ እንደሚያደርጉት ነው ያብራሩት። ፓርኩ ከወንዝ ዳርቻ ልማት ጋር ተሰናስሎ የተሰራ በመሆኑ፣ የአረንጓዴ ልማት መናፈሻውና የውሃ ፋውንቴኑ አዲስ አበባን ለነዋሪዎቿ ምቹ አረንጓዴ ከተማ ለማድረግ የተጀመረውን የኮሪደር ልማት በተግባር የሚያረጋግጥ መሆኑን ገልጸዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ አዲስ ስፖርት ፓርክ የፅናትና የብልጽግና ምልክት መሆኑን ገልጸው ከተማዋን ውብና ለኑሮ ምቹ የማድረግ ጉዞ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል።
ቡናማዎቹ በሊጉ ደረጃቸውን አሻሽለዋል
Apr 4, 2026 122
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ቡና ኢትዮጵያ መድንን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቢኒያም ጌታቸው በ47ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮጵያ ቡና አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ35 ነጥብ ደረጃውን ከዘጠነኛ ወደ ሰባተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በሊጉ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ መድን በ28 ነጥብ ከነበረበት 14ኛ ደረጃ ወደ 15ኛ ዝቅ ብሏል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በውጤት ማጣት ቀውስ ውስጥ ይገኛል።
ማንችስተር ሲቲ ለኤፍኤ ካፕ ግማሽ ፍጻሜ አለፈ
Apr 4, 2026 99
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በኤፍኤ ካፕ የመጀመሪያ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ሊቨርፑልን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሊንግ ሃላንድ ሁለት በጨዋታ እና አንድ በፍጹም ቅጣት ምት ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። አንቶዋን ሴሜኒዮ ቀሪዋን ጎል ለሲቲ ከመረብ ላይ አሳርፏል። የሊቨርፑሉ መሐመድ ሳላህ በ64ኛው ደቂቃ ቡድኑ ያገኘውን ፍጹም ቅጣት ምት ሳይጠቀምበት ቀርቷል። በጨዋታው ማንችስተር ሲቲ ያገኛቸውን የግብ እድሎች በሚገባ መጠቀሙ አሐናፊ አድርጎታል። ውጤቱን ተከትሎ የሰባት ጊዜ የኤፍኤ ካፕ አሸናፊው ማንችስተር ሲቲ ወደ ግማሽ ፍጻሜ አልፏል። የስምንት ጊዜ የዋንጫ ባለቤቱ ሊቨርፑል የዘንድሮ ጉዞው ሩብ ፍጻሜ ላይ ተገቷል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Apr 4, 2026 94
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ቅዱስ ጊዮርጊስ ሀዲያ ሆሳዕናን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ያብስራ ጎሳዬ በመጀመሪያው አጋማሽ ማብቂያ ባስቆጠረው ጎል ቅዱስ ጊዮርጊስ መሪ መሆን ችሏል። የቅዱስ ጊዮርጊሱ ያብስራ ጎሳዬ በ63ኛው ደቂቃ በራሱ ላይ ባስቆጠረው ግብ ሀዲያ ሆሳዕና አቻ ሆኗል። ጨዋታው በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ ሲባል ፉዓድ አብደላ በ93ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አስገኝቷል። ከስምንት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ቅዱስ ጊዮርጊስ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ28 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ወደ 15ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በሊጉ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሀዲያ ሆሳዕና በ29 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች አላሸነፈም።
የአትሌቲኮ ማድሪድ እና ባርሴሎና የላሊጋ የሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታ
Apr 4, 2026 124
አዲስ አበባ፣ መጋቢት 26/2018(ኢዜአ)፡- በስፔን ላሊጋ የ30ኛ ሳምንት መርሐ ግብር አትሌቲኮ ማድሪድ እና ባርሴሎና ዛሬ የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ የእግር ኳስ አፍቃሪያን ትኩረት ስቧል። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ላይ 70 ሺህ 692 ተመልካች በሚያስተናግደው ዋንዳ ሜትሮፖሊታኖ ስታዲየም ይካሄዳል። አትሌቲኮ ማድሪድ በሊጉ እስከ አሁን ካደረጋቸው 29 ጨዋታዎች በ17ቱ ድል ሲቀናው በስድስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ስድስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 49 ግቦችን ሲያስቆጥር 28 ጎሎችን አስተናግዷል። የማድሪዱ ክለብ በ57 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ባርሴሎና በበኩሉ 29 ጨዋታዎችን አከናውኖ በ24ቱ አሸንፎ በአራቱ ሽንፈት አስተናግዶ በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። 78 ጎሎችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 28 ግቦች ተቆጥረውበታል። የካታላኑ ክለብ በ73 ነጥብ ሊጉን እየመራ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በሁሉም ውድድሮች ሲገናኙ የዛሬው ለ254ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ በፊት ባደረጓቸው 253 የእርስ በእርስ ጨዋታዎች ባርሴሎና 116 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። አትሌቲኮ ማድሪድ 81 ጊዜ ድል ቀንቶታል። 56 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በላሊጋው እስከ አሁን 178 ጊዜ ተገናኝተው ባርሴሎና 83 ጊዜ አሸንፏል። አትሌቲኮ ማድሪድ 53 ጊዜ ሲያሸንፍ 42 ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርተዋል። አትሌቲኮ ማድሪድ ማሸነፍ በሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። ባርሴሎና ድል ቀናው የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። በተያያዘም በ69 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ሪያል ማድሪድ ከሜዳው ውጪ ከሪያል ማዮርካ ጋር ከቀኑ 11 ሰዓት ከ15 ላይ ይጫወታል። ዛሬ የሚደረጉ ጨዋታዎች በላሊጋው የዋንጫ ፉክክር ወሳኝ የሚባሉ ናቸው።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከመቀሌ 70 እንደርታ ጋር ይጫወታል
Apr 4, 2026 92
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደርጋሉ። ምሽት 12 ሰዓት ላይ መቀሌ 70 እንደርታ ከሲዳማ ቡና በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቀሌ 70 እንደርታ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 24 ጨዋታዎች በአራቱ አሸንፎ በዘጠኙ ተሸንፎ 11 ጊዜ አቻ ወጥቷል። 15 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያሳርፍ 25 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ23 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና 24 ጨዋታዎችን አከናውኖ 12 ጊዜ ሲያሸንፍ በሶስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ዘጠኝ ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 30 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 12 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሲዳማ ቡና በ45 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ያላሸነፈው መቀሌ 70 እንደርታ ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ለምወጣት በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኛል። ሲዳማ ቡና ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ እና መሪነቱን ለማጠናከር ይጫወታል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ኢትዮጵያ መድን ከኢትዮጵያ ቡና ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ኢትዮጵያ መድን በውድድር ዓመቱ 24 ጨዋታዎችን አድርጎ ስድስቱን ሲያሸንፍ በስምንቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ 10 ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። 19 ግቦችን በ24ቱ ጨዋታዎች ላይ 15 ግቦችን ሲያስቆጥር 18 ጎሎችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ28 ነጥብ 14ተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በሊጉ ካከናወናቸው 23 ጨዋታዎች መካከል ዘጠኙን ያሸነፈው ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ በተመሳሳይ ዘጠኝ ጊዜ ተሸንፏል። አምስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 23 ግቦችን ሲያገባ 24 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀራቸው ቡናማዎቹ በ32 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዘዋል። ሁለቱም ቡድኖች ተከታታይ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። ሀዲያ ሆሳዕና ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀኑ 7 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሀዲያ ሆሳዕና በ29 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ25 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሀዲያ ሆሳዕና ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለፉት ስምንት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሶስት ነጥብ ከዛሬው ጨዋታ ማግኘት ከወራጅ ቀጠና እንዲወጣ ያደርገዋል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ወላይታ ድቻ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ወላይታ ድቻ በ27 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ30 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ24ኛ ሳምንት ከመቀሌ 70 እንደርታ ጋር ያለ ግብ አቻ የተለያየው ወላይታ ድቻ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ድል ከቀናው ከወራጅ ቀጠና ይወጣል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል።
ተጠባቂው የማንችስተር እና ሊቨርፑል የኤፍኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ
Apr 4, 2026 130
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፡- በኤፍኤ ካፕ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 8 ሰዓት ከ45 ላይ ማንችስተር ሲቲ ከሊቨርፑል በኢትሃድ ስታዲየም ይጫወታሉ። በጥሎ ማለፉ ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን፣ ሊቨርፑል ዎልቭስን ማሸነፋቸው ይታወቃል። ሁለቱ ክለቦች በኤፍኤ ካፕ ሲገናኙ የአሁኑ ለዘጠነኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ስምንት ጨዋታዎች ሊቨርፑል በአራቱ ድል ሲቀናው ማንችስተር ሲቲ ሁለት ጊዜ አሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ1897 ሲሆን ሊቨርፑል 2 ለ 1 አሸንፏል። በውድድሩ ላይ ለመጨረሻ ጊዜ የተጫወቱት እ.አ.አ በ2022 በግማሽ ፍጻሜው ሲሆን ሊቨርፑል 3 ለ 2 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። በፍጻሜው ቼልሲን በማሸነፍ ዋንጫውን አንስቷል። ማንችስተር ሲቲ ለመጨረሻ ጊዜ ሊቨርፑልን በኤፍኤ ካፕ ያሸነፈው እ.አ.አ በ2003 ሲሆን በሶስተኛው ዙር 1 ለ 0 አሸንፏል። ሁለቱ ክለቦች በውድድሩ ስኬታማ የሚባሉ ክለቦች ናቸው። ማንችስተር ሲቲ ሰባት ጊዜ ዋንጫውን ሲያነሳ፣ ሊቨርፑል ስምንት ጊዜ ውድድሩን አሸንፏል። ሁለቱ ቡድኖች ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጉት ፍልሚያ የተመልካቾችን ትኩረት ስቧል። በሌላኛው መርሐ ግብር ሳውዝሃምፕተን ከአርሰናል ምሽት 4 ሰዓት ላይ በሴንት ሜሪ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በጥሎ ማለፉ ሳውዝሃምፕተን ፉልሃምን፣ አርሰናል ማንስፊልድ ታውንን በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜ ገብተዋል። ሳውዝሃምፕተን አንድ ጊዜ ውድድሩን አሸንፏል። አርሰናል ዋንጫውን 14 ጊዜ በማንሳት የውድድሩ ስኬታማ ክለብ ነው። ባለሜዳው ሳውዝሃምፕተን በእንግሊዝ ሻምፒዮንሺፕ (ሁለተኛ ዲቪዚዮን) የሚገኝ ሲሆን አርሰናል የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግን እየመራ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች ከዚህ ቀደም በውድድሩ ባደረጓቸው 11 ጨዋታዎች አርሰናል ሰባቱን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ሳውዝሃምፕተን በሶስቱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። ምሽት 1 ሰዓት ከ15 ላይ ቼልሲ ፖርትቫሌን በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ያስተናግዳል። ሁለቱ ክለቦች በኤፍኤ ካፕ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ቼልሲ የፕሪሚየር ሊግ፣ ፖርት ቫሌ የፉትቦል ሊግ ዋን (ሶስተኛ ዲቪዚዮን) ክለቦች ናቸው። የምዕራብ ለንደኑ ቼልሲ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ስምንት ጊዜ አንስቷል። ፖርት ቫሌ በውድደሩ ትልቁ ውጤቱ ግማሽ ፍጻሜ ከመድረስ የዘለለ አይደለም። 154 ዓመታትን ያስቆጠረው ኤፍኤ ካፕ የዓለማችን አንጋፋ የእግር ኳስ ውድድር ነው።
ምድረ ገነት ሽሬ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል
Apr 3, 2026 265
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 25/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መቻል እና ምድረ ገነት ሽሬ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዓለምብርሃን ይግዛው በ50ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል መቻል መሪ ሆኗል። ተካልኝ ዳኜ በ77ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ለምድረ ገነት ሽሬ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። ጨዋታውን ተከትሎ መቻል በ37 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ምድረ ገነት ሽሬ በ28 ነጥብ ደረጃውን ከ17ኛ ወደ 15ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች ድል ማስመዝገብ አልቻለም። ዛሬ ቀን ላይ በተካሄዱ ጨዋታዎች በሊጉ ግርጌ የሚገኘው አርባምንጭ ከተማ ሸገር ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከባህር ዳር ከተማ እና ድሬዳዋ ከተማ ከፋሲል ከነማ ያደረጓቸው ጨዋታዎች ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል።