ቀጥታ፡
ስፖርት
የኢትዮጵያን የስፖርት ቱሪዝም ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው
Jan 23, 2026 81
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የስፖርት ቱሪዝም ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ገለጸ። የስፖርት ቱሪዝም በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ የመጣ የቱሪዝም ዘርፍ ነው። በኢትዮጵያም በአትሌቲክስ፣ በጎዳና ላይ ሩጫ፣ ባሕላዊ እና ሌሎች የጉብኝት ቦታዎች የእግር ጉዞ የስፖርት አይነቶች ለስፖርት ቱሪዝም ተጠቃሚነት ምቹ አቅሞች ናቸው። የኢትዮጵያ የስፖርት ቱሪዝም አቅሞችም በሀገር ገጽታ ግንባታ፣ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን በማሳደግና በስፖርት መሠረተ ልማት ግንባታ ከፍተኛ ፋይዳ አላቸው። የአዲስ አበባና ሌሎች ዋና ዋና ከተሞች የኮሪደር ልማትም በስፖርት ማዘውተሪያ ስታዲየም ግንባታ፣ በብስክሌትና በእግር መንገድ የስፖርት ዘርፎች ለስፖርት ቱሪዝም ዕድገት ወሳኝ ምዕራፍ ከፍተዋል። በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በጥቂት ዓመታት ውስጥ በአዲስ አበባ የተገነቡ መሠረተ ልማቶች ለስፖርት ቱሪዝም እንቅስቃሴ ምቹ ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል። ‎የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴዔታ መኪዩ መሐመድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አዲስ አበባን ለስፖርት ቱሪዝም ምቹ ለማድረግ የተሰሩ ተግባራት ከፍተኛ ውጤት እያስገኙ ነው ብለዋል። በተለይም የመዲናዋ የኮንፍረንስ ቱሪዝም ማዕከልነት እያደገ መምጣት ለስፖርት ቱሪዝም እንቅስቃሴ ወሳኝ ምዕራፍ መክፈቱን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት ሁለት ዓመታት 16 ዓለም አቀፋዊ የስፖርት ሁነቶችን በስኬት በማስተናገድ ኢትዮጵያ ለስፖርት ቱሪዝም አቅም እንዳላት በተግባር ማሳየት እንደተቻለ ተናግረዋል። ለአብነትም በየዓመቱ በርካታ የሀገር ውስጥና የውጭ ዜጎች የሚሳተፉበት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ እና 46ኛው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በስኬት መስተናገዳቸውን አንስተዋል። በኢትዮጵያ በስፖርት ቱሪዝም የሚስተናገዱ ሁነቶችም በሀገር ገጽታ ግንባታና በውጭ ምንዛሬ ገቢ እንዲሁም የስፖርት መሠረተ ልማትን በማስፋፋት አዎንታዊ ሚና እንዳላቸው አብራርተዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያ 32 ብሔራዊ የስፖርት ፌዴሬሽኖች ዓለም አቀፍ የስፖርት ሁነቶችን ወደ ሀገር ውስጥ እንዲያመጡ በትብብር እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ የሚካሄዱትን 5ኛው የአፍሪካ ወጣቶች ኦሎምፒክና የአፍሪካ የባህል ስፖርት ፌስቲቫል ለማስተናገድ በቂ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። የ‎ኢትዮጵያን የስፖርት ዲፕሎማሲ እና ስፖርታዊ ኩነቶች የማስተናገድ አቅም በማሳደግ ቀዳሚ የአፍሪካ የስፖርት ቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያን ማስተዋወቅ አላማ ያደረገው የሐዋሳ ሀይቅ ግማሽ ማራቶን የካቲት 1 ይካሄዳል
Jan 23, 2026 65
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ)፦‎ 14ኛው የሐዋሳ ሀይቅ ግማሽ ማራቶን የካቲት 1 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አስታወቀ። ውድድሩ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከቱሪዝም ሚኒስቴር፣ ኢትዮ ቴለኮም እና ሌሎች ተቋማት ጋር በትብብር የሚያዘጋጀው ነው። በዘንድሮው ውድድር ከአዲስ አበባ እና ከውጭ ሀገራት ወደ ሐዋሳ የሚመጡ ከ500 በላይ ተሳታፊዎች የሚጠበቁ ሲሆን የሐዋሳ ከተማ እና አካባቢዋ ነዋሪዎችን ጨምሮ ወደ አምስት ሺህ የሚጠጉ ተወዳዳሪዎች የሚሳተፉበት ውድድር እንደሚሆን ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ለኢዜአ በላከው መግለጫው አመልክቷል። በተጨማሪም በውድድሩ ላይ ከ21 በላይ ሀገራት እና ከሁሉም አህጉራት የተውጣጡ ተወዳዳሪዎች እንደሚሳተፉ ያመለከተው መግለጫው ይህ ዓለም አቀፋዊ ተሳትፎ ሐዋሳ ያላትን ትልቅ የቱሪስት መዳረሻነት ይበልጥ እንደሚያጠናክር ገልጿል። 14ኛው የሐዋሳ ሀይቅ ግማሽ ማራቶን በስድስት የክልል ከተሞች የሚካሄደው የልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክስ (Discover Ethiopia Classics) ተከታታይ ውድድሮች አካል ነው። ይህ በደብረ ብርሃን ከተማ የተጀመረው የስድስት ከተሞች ውድድር የሀገሪቱን ተፈጥሮ እና ባህል ለሌሎች ለማስተዋወቅ ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑ ተጠቁሟል። ሐዋሳ የዚህ ውድድር ሁለተኛ መዳረሻ ከተማ ስትሆን ጅማ ፣ በቆጂ፣ አርባ ምንጭ እና ሐረር በቀጣዮቹ ወራት ተመሳሳይ የውድድር እና የጉብኝት ቀናት እንደሚኖራቸው ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ያስታወቀው። የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ዋና ስራ አስኪያጅ ዳግማዊት አማረ ስለ የሐዋሳ ሐይቅ ግማሽ ማራቶን ከሩጫው ባለፈ የኢትዮጵያን ተፈጥሯዊ ውበት እና እንግዳ ተቀባይነት የምናከብርበት ዝግጅት ነው ብለዋል። ከቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ሐዋሳን የስፖርት እና የቱሪስት መዳረሻ ማዕከልነቷን ለማሳደግ በትብብር እየተሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል። ሐዋሳ ዓለም አቀፍ አትሌቲክስን ለሚፈልጉ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች ሊጎበኟት የሚገባ መዳረሻ መሆኗ ከዚህ ቀደም በተካሄዱ ውድድሮች መታዩትን አውስተዋል። ዝግጅቱ ከዋናው የ21 ኪሎ ሜትር ውድድር በተጨማሪ የ8 ኪሎ ሜትር የህዝብ ሩጫ እና የህፃናት ሩጫዎችን የሚያካትት ነው። ከሩጫውም ባለፈ በታቦር ተራራ ላይ የሚደረግ የእግር ጉዞ እና ልዩ የቱሪስት መስህቦችን ጉብኝት እንደሚደረግ ተገልጿል። በስድስት የክልል ከተሞች የሚካሄደው የልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክስ (Discover Ethiopia Classics) ጥር 3 ቀን 2018 ዓ.ም በደብረ ብርሃን በተካሄደ ውድድር መጀመሩ የሚታወስ ነው።
በክልሉ 5ኛው ክልል አቀፍ የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫልና የስፖርት ውድድር መካሄድ ጀመረ
Jan 22, 2026 84
ቦንጋ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል 5ኛው ክልል አቀፍ የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫልና ልዩ ልዩ ስፖርቶች ውድድር በቦንጋ ከተማ መካሄድ ጀመረ። ውድድሩ "ስፖርታችን ለኢትዮጵያ እድገት ማንሰራራት" በሚል መሪ ሀሳብ ከጥር 14 እስከ 19 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ እንደሚካሄድ ታውቋል።   በውድድሩ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በክልሉ በሀገርና በዓለም መድረክ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት በትኩረት መስራት ይገባል። ውድድሩ በአዕምሮና በአካል ብቁ ዜጋ ለማፍራት ካለው ፋይዳ ባሻገር ሀገርን ወክለው በዓለም አደባባይ የሚሳተፉ ስፖርተኞችን ጭምር ለማፍራት ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸዋል። ለዚህም በየአካባቢው ለወጣቶች ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር መስራት እንደሚገባ ጠቁመው የክልሉ መንግስትም የስፖርት ዘርፉን ለማገዝ ቁርጠኛ መሆኑን ተናግረዋል።   ፌስቲቫሉና ውድድሩ በተለይም ተዘንግተው የቆዩ የባህል ስፖርቶችን አውጥቶ ለትውልድ ከማስተላለፍና የእርስ በርስ ትስስርን ከማጠናከር አንጻር ፋይዳው የጎላ መሆኑንም አመልክተዋል።   የክልሉ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ሀላፊ ፋንታሁን ብላቴ በበኩላቸው ስፖርት ለህዝቦች ትስስርና አንድነት መጠናከር ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ነው ብለዋል። ከዛሬ ጀምሮ ለተከታታይ ስድስት ቀናት የሚካሄደው ውድድር ታዳጊ ስፖርተኞች የሚመለመሉበትና የባህል ልውውጥ የማደረግበት መሆኑንም ተናግረዋል። ውድድሩ በ11 የስፖርት ዓይነቶች የሚካሄድ ሲሆን በታዳጊ ወጣቶች ምዘና ውድድር ላይ የሚሳተፉ ብቁ ስፖርተኞችም እንደሚመለመሉ ታውቋል። በውድድሩ ቤንች ሸኮ ዞን ከምዕራብ ኦሞ ዞን ባደረጉት የእግር ኳስ ውድድር የተጀመረ ሲሆን፣ ከክልሉ ሁሉም ዞኖች የተውጣጡ ከ600 በላይ ስፖርተኞች እንደሚሳተፉ ተመላክቷል።
ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን በማሸነፍ መሪነቱን አጠናከረ
Jan 22, 2026 86
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018 (ኢዜአ)፦‎ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 3 ለ 0 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብለስ ናጎ፣ ፍራኦል መንግስቱ እና ዮሴፍ ዮሐንስ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሲዳማ ቡና በ33 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ቡና በ19 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ-ግብር መቻል ቅዱስ ጊዮርጊስን 2 ለ 0 አሸንፏል። ፈቱዲን ጀማል የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉን ያስመዘገበው መቻል በ26 ነጥብ ደረጃውን ከ7ኛ ወደ 3ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ22 ነጥብ ከነበረበት 8ኛ ደረጃ ወደ 9ኛ ዝቅ ብሏል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ እና ኢትዮጵያ መድን ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ16ኛ ሳምንት መርሐ- ግብር ተጠናቋል። የ17ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከጥር 17 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄዱ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
የሊጉ መሪ  ሲዳማ ቡና እና ኢትዮጵያ ቡና የሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታ 
Jan 22, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ ቡና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል። ሲዳማ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው 15 ጨዋታዎች መካከል ስምንቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በስድስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ15ቱ ጨዋታዎች ላይ 20 ጎሎችን ሲያስቆጥር ስምንት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ30 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና 15 ጨዋታዎችን አከናውኖ በአምስቱ አሸንፎ በስድስቱ ተሸንፎ አራት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 14 ግቦችን ሲያስቆጥር 15 ጎሎችን አስተናግዷል። ኢትዮጵያ ቡና በ19 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ሲዳማ ቡና ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። ኢትዮጵያ ቡና ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በሌላኛው መርሃ ግብር መቻል ከቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። መቻል እስከ አሁን በሊጉ 15 ጨዋታዎችን አድርጎ ስድስት ጊዜ ሲያሸንፍ በአራቱ ተሸንፏል። በስድስቱ ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 20 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያስቆጥር 13 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ23 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ ባከናወናቸው 15 ጨዋታዎች በስድስቱ ሲያሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። አራት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 15 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 10 ግቦች ተቆጥረውበታል። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ22 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ሁለቱ ቡድኖች በሊጉ ተከታታይ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ድሬዳዋ ከተማ ከኢትዮጵያ መድን በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ድሬዳዋ ከተማ በ18 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ17 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ድሬዳዋ ከተማ በቅዱስ ጊዮርጊስ የ4 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። መድን በበኩሉ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ሁለቱ ቡድኖች ወደ ድል መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል።
ባየር ሙኒክ በሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅሏል
Jan 22, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መርሐ-ግብር ባየር ሙኒክ ዩኒየን ሴይንት ጂልዋን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሃሪ ኬን በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሃሪ ኬን በሻምፒዮንስ ሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ ሰባት አድርሷል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት በሁሉም ውድድሮች ያገባቸውን ግቦች ወደ 34 ከፍ አድርጓል። የባየር ሙኒኩ ሚን-ጄ ኪም በ63ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ውጤቱን ተከትሎ ባየር ሙኒክ በ18 ነጥብ ከአርሰናል በመቀጠል ጥሎ ማለፍ የገባ ሁለተኛው ክለብ ሆኗል። በደረጃ ሰንጠረዡ ሁለተኛ ላይ ይገኛል። የቤልጂየሙ ዩኒየን ሴይንት ጊልዋ በስድስት ነጥብ 31ኛ ደረጃን ይዟል። በሌሎች ጨዋታዎች ሊቨርፑል ማርሴይን 3 ለ 0 አሸንፏል። ዶምኒክ ስቦዝላይ፣ ኮዲ ጋፕኮ እና የማርሴይ ግብ ጠባቂ ጄሮኒሞ ሩሊ በራሱ ላይ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሊቨርፑል በ15 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ማርሴይ በዘጠኝ ነጥብ 19ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቼልሲ ፓፎስን በሞሰስ ኬይስዶ ግብ 1 ለ 0 ረቷል። ባርሴሎና ከሜዳው ውጪ ስላቪያ ፕራግን 4 ለ 2 አሸንፏል። ፌርሚን ሎፔዝ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ዳኒ ኦልሞ እና ሮበርት ሌዋንዶስኪ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቫሲል ኩሴጅ እና የባርሴሎና ሮበርት ሌዋንዶውስኪ በራሱ ላይ ለስላቪያ ፕራግ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኒውካስትል ዩናይትድ በአሮን ዊሳ፣ አንቶኒ ጎርደን እና ሃርቪ ባርንስ ግቦች ፒኤስቪ አይንድሆቨንን 3 ለ 0 አሸንፏል። ጁቬንቱስ ቤኔፊካን 2 ለ 0፣ አትሌቲኮ ቢልባኦ አትላንታን 3 ለ 2 አሸንፈዋል። የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የመጨረሻ መርሐ-ግብር በቀጣይ ሳምንት ይደረጋል።
አዳማ ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Jan 21, 2026 72
አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2018 (ኢዜአ)፦‎ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ16ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር አዳማ ከተማ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 3 ለ 2 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቢኒያም አይተን እና አቡበከር ሳኒ በጨዋታ አህመድ ሁሴን በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አዲስ ግደይ እና ዩጋንዳዊው ሳይመን ፒተር የንግድ ባንክን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ከሶስት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው አዳማ ከተማ በ26 ነጥብ ደረጃውን ከ7ኛ ወደ 4ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በሊጉ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ17 ነጥብ ከነበረበት 13ኛ ደረጃ ወደ 14ኛ ዝቅ ብሏል። ቡድኑ ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ አጥቂ አዲስ ግደይ በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ ስምንት ከፍ በማድረግ ተመሳሳይ የግብ መጠን ካለው የቅዱስ ጊዮርጊሱ አቤል ያለው ጋር የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በጋራ መምራት ጀምሯል።
በሻምፒዮንስ ሊጉ ባየር ሙኒክ ከዩኒየን ሴይንት-ጂሎይስ ጋር ይጫወታል
Jan 21, 2026 102
አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዛሬ ዘጠኝ ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም ምሽት አምስት ሰዓት ላይ ባየር ሙኒክ ከዩኒየን ሴይንት-ጂሎይስ ጋር ይጫወታል። የስድስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ባየር ሙኒክ በ15 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በሻምፒዮንስ ሊጉ ኢንተር ሚላን ከአርሰናል የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው አርሰናል በሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፍ የገባ የመጀመሪያ ቡድን ሆኗል በውድድሩ ላይ የመጀመሪያ ተሳትፎውን እያደረገ የሚገኘው ዩኒየን ሴይንት-ጂሎይስ በስድስት ነጥብ 30ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ክለቦች በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ባየር ሙኒክ ጨዋታውን የማሸነፍ ሰፊ ግምት ያገኘ ሲሆን፤ ሶስት ነጥብ ማግኘት ወደ ጥሎ ማለፍ የመግባት እድሉን ያሰፋዋል።   በሌሎች መርሐ-ግብሮች ማርሴይ ከሊቨርፑል፣ ቼልሲ ከፓፎስ፣ ስላቪያ ፕራግ ከባርሴሎና፣ ጁቬንቱስ ከቤኔፊካ፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ከፒኤስቪ አይንድሆቨን እና አትላንታ ከአትሌቲኮ ቢልባኦ በተመሳሳይ ምሽት አምስት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሻምፒዮንስ ሊጉ ማንችስተር ሲቲ በቦዶ ግሊምት ያልተጠበቀ ሽንፈት አስተናገደ ጋላታሳራይ ከአትሌቲኮ ማድሪድ እና ካራባግ ከኢንትራክት ፍራንክፈርት በተመሳሳይ ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ላይ ይጫወታሉ።
ሐዋሳ ከተማ ከነገሌ አርሲ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 21, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ጥር 13 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 12 ሠዓት ሐዋሳ ከተማ ከነገሌ አርሲ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሐዋሳ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 15 ጨዋታዎች በሰባቱ አሸንፎ በአራቱ ተሸንፎ በአራቱ አቻ ወጥቷል። በ15ቱ ጨዋታዎች 16 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 10 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ25 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ነገሌ አርሲ በሊጉ 15 ጨዋታዎች አከናውኖ ሰባት ጊዜ ድል ሲቀናው በሶስቱ ተሸንፏል። አምስት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። 17 ግቦችን ሲያስቆጥር 10 ጎሎችን አስተናግዷል። አዲስ አዳጊው ነገሌ አርሲ በ26 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው ሁለቱ ክለቦች ከ15ኛ ሳምንት የአቻ ውጤታቸው በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። በሌላኛው መርሐ-ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከአዳማ ከተማ ቀን 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እስከ አሁን በሊጉ ማሸነፍ የቻለው ጨዋታ ብዛት ሶስት ብቻ ነው። አራት ጊዜ ሲሸነፍ ስምንት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 17 ግቦችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ 17 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ17 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ በበኩሉ 15 ጨዋታዎችን አድርጎ አምስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በስምንት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 11 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 9 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዳማ ከተማ በ23 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ15ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር በኢትዮ ኤሌክትሪክ የ2 ለ1 ሽንፈት አስተናግዷል። አዳማ ከተማ ባለፉት ሶስት የሊጉ ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ምድረ ገነት ሽሬ ከአርባ ምንጭ ከተማ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረ ገነት ሽሬ በ17 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አርባ ምንጭ ከተማ በስምንት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ምድረ ገነት ሽሬ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። አርባ ምንጭ ከተማ በሊጉ ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው። ጨዋታው ምድረ ገነት ሽሬ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ አርባ ምንጭ ከተማ የመጀመሪያ ሶስት ነጥቡን ለማግኘት የሚያደርጉት ነው። ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። በደረጃ ሰንጠረዡ ወልዋሎ ዓዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ12 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሸገር ከተማ በ15 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሁለቱም ቡድኖች በተመሳሳይ ባለፉት ስድስት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻሉም። ሶስት ነጥብ ለሁለቱም ወሳኝ ነው።
አርሰናል በሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፍ የገባ የመጀመሪያ ቡድን ሆኗል
Jan 21, 2026 94
አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጠባቂ መርሐ-ግብር አርሰናል ኢንተር ሚላንን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በሳንሲሮ ስታዲየም በተካሄደ ጨዋታ ጋብርኤል ጄሱስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ተቀይሮ የገባው ቪክቶር ዮኬሬስ ቀሪዋን ጎል ከመረብ አሳርፏል። ፔታር ሱቺች ለኢንተር ሚላን ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ አርሰናል በ21 ነጥብ አንድ ጨዋታ እየቀረው ጥሎ ማለፉን የተቀላቀለ የመጀመሪያ ቡድን ሆኗል። አርሰናል በዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ ሁሉንም ጨዋታዎች ያሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው። በውድድሩ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢንተር ሚላን በ12 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። በሌሎች መርሐ-ግብሮች የ15 ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሪያል ማድሪድ ሞናኮን በሜዳው 6 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ኪሊያን ምባፔ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ፍራንኮ ማስታንቱኖ፣ ቪኒሺየስ ጁኒየር፣ ጁድ ቤሊንግሃም እና የሞናኮው ቲሎ ኬህረር በራሱ ላይ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጆርዳን ቴዜ ለሞናኮ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ሪያል ማድሪድ በ15 ነጥብ ሶስተኛ፣ ሞናኮ በዘጠኝ ነጥብ 20ኛ ደረጃን ይዘዋል። ስፖርቲንግ ሊዝበን የወቅቱን የዋንጫ ባለቤት ፒኤስጂን ሳይጠበቅ 2 ለ 1 አሸንፏል። ሉዊስ ሱዋሬዝ ለስፖርቲንግ ሊዝበን ሁለቱን ግቦች ሲያስቆጥር ክቪቻ ክቫርትስኬሊያ ለፒኤስጂ ብቸኛውን ጎል ከመረብ አሳርፏል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ ቦሩሲያ ዶርትሙንድን 2 ለ 0 ሲረታ ክርስቲያን ሮሜሮ እና ዶምኒክ ሶላንኬ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። የቦሩሲያ ዶርትሙንዱ ዳንኤል ስቬንሰን በ24ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ኮፐንሃገን እና ናፖሊ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ጆርዳን ላርሰን ለኮፐንሃገን፣ ስኮት ማክቶሚናይ ለናፖሊ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የኮፐንሃገኑ ቶማስ ዴላኒ በ35ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ኦሎምፒያኮስ ባየር ሌቨርኩሰንን 2 ለ 0 ሲረታ አያክስ ቪያሪያልን 2 ለ 1 አሸንፏል።
በሻምፒዮንስ ሊጉ ማንችስተር ሲቲ በቦዶ ግሊምት ያልተጠበቀ ሽንፈት አስተናገደ
Jan 20, 2026 107
አዲስ አበባ፤ ጥር 12/2018 (ኢዜአ)፦‎ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መርሐ ግብር የኖርዌዩ ቦዶ ግሊምት ማንችስተር ሲቲን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአስፕማይራ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ካስፐር ዋርትስ ሆግ ሁለት ጎሎችን ሲያስቆጥር ጄንስ ፒተር ሃውግ ቀሪዋን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ራያን ቸርኪ ለሲቲ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል።   የማንችስተር ሲቲው አማካይ ሮድሪ በ62ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በጨዋታው ማንችስተር ሲቲ ከፍተኛ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ቦዶ ግሊምት ግልጽ የግብ እድሎችን በመፍጠር የተሻለ ነበር። በውድድሩ ሁለተኛ ድሉን ያስመዘገበው ቦዶ ግሊምት በስድስት ነጥብ ደረጃውን ከ32ኛ ወደ 26ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በሻምፒዮንስ ሊጉ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ማንችስተር ሲቲ በ13 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ሲቲ በሁሉም ውድድሮች ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። በተያያዘም ማምሻውን በተደረገ ሌላኛው መርሐ-ግብር ክለብ ብሩዥን ካይራት አልማቲን 4 ለ 1 ረቷል። ምሽት አምስት ላይ በሳን ሲሮ ስታዲየም ኢንተር ሚላን ከአርሰናል የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
መቀሌ 70 እንደርታ ኢትዮ ኤሌክትሪክን በማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና የወጣበትን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Jan 20, 2026 87
አዲስ አበባ፤ ጥር 12/2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ16ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር መቀሌ 70 እንደርታ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጊት ጋትኩት እና ፍፁም አለሙ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሀብታሙ ሸዋለም ለኢትዮ ኤሌክትሪክ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ድሉን ያስመዘገበው መቀሌ 70 እንደርታ በ16 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ወደ 16ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። በአንጻሩ በሊጉ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ25 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረገ የ16ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ወላይታ ድቻ እና ባህር ዳር ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም ፋሲል ከነማ ከሀዲያ ሆሳዕና ዛሬ ሊያደርጉት የነበረው ጨዋታ በበዓሉ ምክንያት ያልተካሄደ ሲሆን በቀጣይ በሚገለጽ ጊዜ በተስተካካይ መርሃ ግብር እንደሚደረግ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊዋ ሴኔጋል በፊፋ የዓለም ሀገራት ወርሃዊ ደረጃ ወደ 12ኛ ደረጃ ከፍ አለች
Jan 20, 2026 93
አዲስ አበባ፤ ጥር 12/2018(ኢዜአ):- የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር(ፊፋ) ወርሃዊ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃን ይፋ አድርጓል። በዚህም የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ባለድሏ ሴኔጋል ሰባት ደረጃዎችን በማሻሻል ከነበረችበት 19ኛ ደረጃ ወደ 12ኛ ከፍ ብላለች።   በፍጻሜው ሽንፈት ያስተናገደችው ሞሮኮ ደግሞ ከ11ኛ ወደ 8ኛ ከፍ ብላለች። በውድድሩ ሶስተኛ ደረጃ ይዛ ያጠናቀቀችው ናይጄሪያ 12 ደረጃዎችን በማሻሻል 26ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። አልጄሪያ 28ኛ፣ ግብጽ 31ኛ፣ ኮትዲቯር 37ኛ፣ ካሜሮን 45ኛ፣ ቱኒዚያ 47ኛ፣ ማሊ 54ኛ፣ ደቡብ አፍሪካ 60ኛ እና ቡርኪና ፋሶ 62ኛ ደረጃን ይዘዋል። ኢትዮጵያ በታህሳስ ወር በነበረችበት 147ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች።   ስፔን፣ አርጀንቲና፣ ፈረንሳይ፣ እንግሊዝ እና ብራዚል ከአንደኛ እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል። ፖርቹጋል እና ኔዘርላንድስ ስድስተኛ እና ሰባተኛ ደረጃ ላይ ሲገኙ ሳን ማሪኖ የመጨረሻውን 210ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። የቡድን ጥንካሬ፣ የሚደረገው ጨዋታ ያለው ወሳኝነት፣ የጨዋታ ውጤትና ከጨዋታ በፊት የሚጠበቅ ውጤት ፊፋ የሀገራትን የእግር ኳስ ደረጃ የሚለከባቸው መመዘኛዎች ናቸው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም