ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ሲዳማ ቡና የሊጉን መሪነት ያጠናከረበት ወሳኝ ድል አስመዘገበ
Apr 19, 2026 409
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ28ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አቤል ያለው ግቦቹን አስቆጥሯል። በሊጉ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በ54 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ መቻል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ 10 ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ32 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ 14 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን አጠናክሯል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር መቻል እና ሃዋሳ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። መቻል በ44 ነጥብ ሁለተኛ፣ ሃዋሳ ከተማ በ43 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። ነገሌ አርሲ ከሀድያ ሆሳዕና አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኪቲካ ጅማ ለነገሌ አርሲ፣ ተመስገን ብርሃኑ ለሀድያ ሆሳዕና ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ነገሌ አርሲ በ44 ነጥብ ሶስተኛ፣ ሀድያ ሆሳዕና በ34 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ዛሬ በአዲስ አበባ ስታዲየም አስቀድሞ የተካሄደው የኢትዮጵያ ቡና እና አርባምንጭ ከተማ ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። ቢንያም ጌታቸው ለኢትዮጵያ ቡና፣ ይድነቃቸው ያሲን ለአርባምንጭ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ኢትዮጵያ ቡና በ38 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ24 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ባየር ሙኒክ የቡንድስሊጋ ዋንጫን ለ35ኛ ጊዜ ማንሳቱን አረጋገጠ
Apr 19, 2026 230
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- በጀርመን ቡንድስሊጋ 30ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ባየር ሙኒክ ስቱትጋርትን 4 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሃሪ ኬን፣ ኒኮላስ ጃክሰን፣ አልፎንሶ ዴቪስ እና ራፋኤል ጉሬሮ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ቼማ አንድሬስ እና ክሪስ ፉህሪች ለስቱትጋርት ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሊጉ 25ኛ ድሉን ያስመዘገበው ባየር ሙኒክ አራት ጨዋታ እየቀረው የቡንደስሊጋ ዋንጫን ማንሳቱን አረጋግጧል። ለ35ኛ ጊዜ ጊዜ ቡንድስሊጋውን በማሸነፍ የጀርመን የበላይነቱን አስመስክሯል። ሙኒክ ካለፉት 15 የቡንድስሊጋ ዋንጫዎች 14ቱን አንስቷል።
የኢትዮጵያ ዘመናዊ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ለአፍሪካ አርአያ ናቸው
Apr 19, 2026 517
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ዘመናዊ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ለቀሪዎቹ አፍሪካ ሀገራት ትልቅ ተምሳሌት ያለው በመሆኑ ተሞክሮውን ሊቀስሙ ይገባል ሲሉ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት አትሌቶች ገለጹ። በአዲስ አበባ ለመጀመሪያ ጊዜ በተካሄደው የ2026 ዓለም አቀፍ የአንድ ቀን የግራንድ ፕሪክስ ውድድር ላይ የተሳተፉ ስመ ጥር አትሌቶች፣ በከተማዋ የተገነቡ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ጎብኝተዋል። አትሌቶቹ የዓድዋ ድል መታሰቢያን፣ የአዲስ ስፖርት ፓርክን እና የወንዝ ዳርቻ ልማትን ተዘዋውረው የተመለከቱ ሲሆን፤ በተገነቡት መሠረተ ልማቶች ጥራትና ውበት መደነቃቸውን ገልጸዋል። በተለይም ኢትዮጵያ ለአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት መሆኗን ያስታወሱት አትሌቶቹ፣ በታሪካዊቷ ከተማ አዲስ አበባ በመገኘታቸው ላቅ ያለ ኩራት እንደተሰማቸው በአጽንኦት ገልጸዋል። የዚምባብዌ አትሌት አሽሊ ቲናሼ ሚለር፤ የታላላቅ አትሌቶች መፍለቂያ በሆነችው ኢትዮጵያ፣ መንግስት ለስፖርቱ ዘርፍ የሰጠው ትኩረት እጅግ የሚያስደስት እና ለሌሎች ሀገራት ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን ተናግራለች። የቦትስዋናው አትሌት ሌትልሆጎኖሎ ሞክጌቲ ፤የስፖርት ማዘውተሪያዎቹ ዘመናዊና የተሟላ ግብዓት ያላቸው መሆናቸው ቀልቡን እንደሳበው በመግለጽ፣ እንዲህ ያሉ መሰረተ ልማቶች የአፍሪካ አትሌቶች በዓለም አቀፍ መድረክ ተወዳዳሪነታቸውን ለማሳደግ ወሳኝ እንደሆኑ ተናግሯል። የሴኔጋል አትሌት ሩጊ ሶው፤ በኢትዮጵያ የታዩት የስፖርት መሠረተ ልማቶች ዘመናዊና አቅምን የሚያሳድጉ በመሆናቸው፣ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በሞዴልነት ሊወሰዱ እንደሚችሉ አስረድታለች። የኬንያ አትሌት ፓሊን ሙርጋ፤ እንዲህ ያሉ ድንቅ የስፖርት ማዘውተሪያዎች በየስፍራው ሊገነቡ እንደሚገባ አመልክታ በዚህም የሀገርን ገጽታ በስፖርት መገንባት እንደሚቻል ገልጻለች። በአጠቃላይ አትሌቶቹ፣ በከተማ ልማትና በስፖርት መሠረተ ልማት ረገድ ኢትዮጵያ እያሳየችው ያለው ፈጣን ለውጥ ለቀጣዩ የአፍሪካ ትውልድ ትልቅ ተስፋ የሚሰጥ መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይም በአዲስ ስፖርት ፓርክ ውስጥ ሀውልት የቆመላቸውን ታዋቂ አትሌቶች በመመልከት ወጣቱ ትውልድ "እኔስ መቼ ነው የሀገሬን ስም በዓለም አደባባይ የማስጠራው" የሚል በጎ የቁጭት ስሜት እንዲያድርበትና ለላቀ ስኬት እንዲነሳሳ የሚያደርግ መሆኑም አትሌቶቹ ተናግረዋል።
የዋንጫውን መዳረሻ ይወስናል በተባለው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ አርሰናልን አሸነፈ
Apr 19, 2026 127
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር ማንችስተር ሲቲ አርሰናልን 2 ለ 1አሸንፏል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ራያን ቸርኪ እና አርሊንግ ሃላንድ ለውሃ ሰማያዊዎቹ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ካይ ሃቫርትዝ ለአርሰናል ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ማንችስተር ሲቲ የተሻለ ብልጫ ነበረው። አርሰናል በጨዋታው ያገኛቸውን ግልጽ የግብ እድሎች አልተጠቀመም። በሊጉ 20ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ በ67 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሶስት ዝቅ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርሰናል በ70 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የዛሬው ውጤት በሁለቱ ክለቦች መካከል ያለውን የዋንጫ ፉክክር ይበልጥ አጓጊ አድርጎታል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች በመርሲሳይድ ደርቢ ሊቨርፑል ኤቨርተንን 2 ለ 1 አሸንፏል። አስቶንቪላ ሰንደርላንድን 4 ለ 3፣ ኖቲንግሃም ፎረስት በርንሌይን 4 ለ 1 አሸንፈዋል። የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ነገ ክሪስታል ፓላስ ከዌስትሃም ዩናይትድ በሚያደርጉት ጨዋታ ይጠናቀቃል።
ሊቨርፑል፣ ኖቲንግሃም ፎረስት እና አስቶንቪላ ተጋጣሚዎቻቸውን አሸንፈዋል
Apr 19, 2026 133
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- በ33ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ሦስት ጨዋታዎች ተካሂደዋል። በመርሲሳይድ ደርቢ ከኤቨርተን ጋር ጨዋታውን ያደረገው ሊቨርፑል 2 ለ 1 ሲያሸንፍ፤ ሞሀመድ ሳላህ እና ቨርጂል ቫንዳይክ ለሊቨርፑል እንዲሁም ቤቶ ለኤቨርተን ግቦቹን አስቆጥረዋል፡፡ በሌላ የጨዋታ መርሐ-ግብር በቪላ ፓርክ ስታዲየም ሰንደርላንድን ያስተናገደው አስቶን ቪላ 4 ለ 3 ረትቷል። በዚህ ጨዋታ ኦሌ ዋትኪንስ (2)፣ ሞርጋን ሮጀርስ እና ታሚ አብርሃም ለአስቶንቪላ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። እንዲሁም ክሪስ ሪግ፣ ትራይ ሀም እና ዊልሰን ኢስዶር የሰንደርላንድን ግቦች አስቆጥረዋል፡፡ ኖቲንግሃም ፎረስት ደግሞ በርንሌይን 4 ለ 1 ማሸነፍ ችሏል።
ኢትዮጵያ ደቡብ ሱዳንን 6 ለ 0 አሸነፈች
Apr 19, 2026 114
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- ለ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ኢትዮጵያ ደቡብ ሱዳንን 6 ለ 0 አሸንፋለች። ጨዋታው ዛሬ 10 ሠዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተካሂዷል። ግቦቹን ያስቆጠሩትም፤ ሲርያ ተሾመ፣ ምኅረት አየለ (3) እንዲሁም ሊያን ዳንኤል (2) ናቸው። በድምር ውጤትም ኢትዮጵያ ደቡብ ሱዳንን 8 ለ0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት ረትታለች። ውጤቱን ተከትሎም ኢትዮጵያ በቀጣይ ከቡርንዲ ጋር እንደምትጫዎት የወጣው መርሐ ግ-ብር ያመላክታል።
የመዲናዋ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ዓለም አቀፍ ውድድሮችን የማስተናገድ ደረጃ ላይ መድረሳችንን ያሳያሉ-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 19, 2026 508
አዲስ አበባ፣ሚያዚያ 11/ 2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ ከተማ የተገነቡ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ውድድሮችን የማስተናገድ ደረጃ ላይ መድረሳችንን የሚያሳዩ ናቸው ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፡፡ ከንቲባ አዳነች በአዲስ አበባ የተገነቡ ዘመናዊ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ውጤት ኢትዮጵያ በአትሌቲክስ ዘርፍ ያላትን ታላቅ ዝና ዳግም ለማረጋገጥ እድል የሰጠ ነው ብለዋል፡፡ የተገነቡት የስፖርት መሰረተ ልማቶች መዲናችን ማንኛውንም ዓይነት ዓለም አቀፍ ውድድር የማስተናገድ ብቃትና ደረጃ ላይ መድረሷን የሚያሳዩ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በአዲስ አበባ የሚከናወኑ ውድድሮች ተተኪ አትሌቶችን ከማነቃቃት ባለፈ ለስፖርት ቱሪዝም ዕድገት የጎላ ፋይዳ እንዳላቸው አስረድተዋል፡፡ ከተማዋን ለነዋሪዎቿ ምቹና ሳቢ ከማድረግ ባሻገር ለዓለም አቀፍ ኩነቶች የስበት ማዕከል መሆኗን በተግባር ማሳየት ተችሏል ነው ያሉት ከንቲባዋ፡፡ ዓለም አቀፍ እና አህጉር አቀፍ መድረኮችን ማዘጋጀት ሀገራዊ አንድነትን በማጠናከር ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለውም አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡
አርባምንጭ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና ነጥብ ተጋሩ
Apr 19, 2026 111
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት አርባምንጭ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቢንያም ጌታቸው በ16ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ግብ ኢትዮጵያ ቡና መሪ ሆኗል። ከእረፍት መልስ ይድነቃቸው ያሲን በ67ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ለአርባምንጭ ከተማ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። ውጤቱን ተከትሎ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው ኢትዮጵያ ቡና በ38 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ24 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ሁለቱ ቡድኖች በተመሳሳይ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፉም።
የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን የማስተናገድ ብቃቷን ያሳየችበት መድረክ ነው
Apr 19, 2026 313
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድር ኢትዮጵያ ግዙፍ ስፖርታዊ ኹነቶችን የማስተናገድ አቅምና ብቃት እንዳላት በተግባር ያሳየችበት መድረክ መሆኑን የኢትዮጵያ ዝነኛ አትሌቶች ገለጹ። ኢትዮጵያ በ2027 የዓለም አትሌቲክስ የወርቅ ደረጃ ውድድርን እንድታስተናግድ ዕድል በማግኘቷ ደስታ እንደተሰማቸውም ጠቅሰዋል። የዓለም አትሌቲክስ የአንድ ቀን ውድድር የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ ስታዲየም ትላንት በስኬት ተካሂዷል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ምክትል ፕሬዚዳንት አትሌት መሰረት ደፋር እንደገለጸችው፣ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ለበርካታ ዓመታት በተለያዩ የዓለም ሀገራት በመዘዋወር ሲወዳደሩ ቆይተዋል። እንዲህ ያሉ ውድድሮች በሀገራችን እንዲካሄዱ የነበረው ምኞት ዛሬ እውን በመሆኑ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማት ተናግራለች። የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ውድድር መካሄዱ ለአትሌቶቻችን ትልቅ መነቃቃትን ፈጥሯል ነው ያለችው። ኢትዮጵያ ማንኛውንም ዓለም አቀፍ የውድድር መድረክ በብቃት ማስተናገድ እንደምትችል ለዓለም ያስመሰከረችበት መሆኑንም አትሌት መሠረት ገልጻለች። በተመሳሳይ ታዋቂው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ውድድሮች እንዲኖሯት የሁልጊዜ ምኞቱ መሆኑን ያስታውሳል። የዓለም አትሌቲክስ የአንድ ቀን ውድድር የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ መካሄዱ የረጅም ጊዜ ህልሙን ያሳካ መሆኑን ገልጿል። ኢትዮጵያ ውድድሩን በስኬት ማስተናገዷ ለሀገር ትልቅ ኩራት መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ኢንጅነር ጌቱ ገረመው ናቸው። ከዚህም ባለፈ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሌሎች ውድድሮችን ለማስተናገድ በር የከፈተና ሀገራችን ትልቅ አመኔታ እንድታገኝ ያደረገ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይ የተሻሉ ዕድሎችን ለመጠቀም በስፖርት መሰረተ ልማትና በዝግጅት ረገድ ጠንክሮ መስራት እንደሚገባ አመላክተዋል። አትሌት መሰረት ደፋር እና አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ መንግሥት ኢትዮጵያ በአትሌቲክስ ያላትን ገናና ስም ለማስቀጠል ለዘርፉ ለሰጠው ትኩረት ምስጋና አቅርበዋል። የተጀመሩ የስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉም ጠይቀዋል። በታሪካዊው የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ውድድር ላይ ከ70 በላይ ዓለም አቀፍ አትሌቶች ተሳታፊ መሆናቸው ታውቋል።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከድሬዳዋ ከተማ ይጫወታል
Apr 19, 2026 87
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ዛሬ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ሲዳማ ቡና ድሬዳዋ ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና በ51 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ድሬዳዋ በ32 ነጥብ 15ኛ ይዟል። በ27ኛው ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 1 ለ 0 የረታው ሲዳማ ማሸነፍ መሪነቱን እንዲያጠናክር ያስችለዋል። በመቻል በ27ኛው ሳምንት 2 ለ 1 የተሸነፈው ድሬዳዋ ከተማ ወደ ድል መንገድ ለመመለስ ይጫወታል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ መቻል ከሃዋሳ ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ የሚያደርጉት ጨዋታ የሚጠበቅ ነው። መቻል በ43 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሃዋሳ ከተማ በ42 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በጥሩ ወቅታዊ ብቃት ላይ የሚገኘው መቻል ማሸነፍ በድል ጉዞው እንዲቀጥል ከማስቻሉ ባሻገር ወደ በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። ባለፉት አራት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ በበኩሉ በዋንጫ ፉክክሩ ለመቆየት ማሸነፍ ግድ ይለዋል። በሌላኛው መርሐ ግብር ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ነገሌ አርሲ ከሀድያ ሆሳዕና በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ነገሌ አርሲ በ43 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟልል። ሀድያ ሆሳዕና በ33 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አቻ የወጣው ነገሌ አርሲ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ማሸነፍ በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በ27ኛ ሳምንት ከኢትዮጵያ ቡና ጋር ሁለት አቻ የወጣው ሀድያ ሆሳዕና ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። ኢትዮጵያ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ኢትዮጵያ ቡና በ37 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ23 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ቡድኖች በተመሳሳይ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፉም። ቡድኖቹ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከደቡብ ሱዳን ጋር ይጫወታል
Apr 19, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በ10ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የአፍሪካ ዞን ቅድመ ማጣሪያ ኢትዮጵያ የመልስ ጨዋታዋን ዛሬ ከደቡብ ሱዳን ጋር ታደርጋለች። ጨዋታው ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳል። ሁለቱ ሀገራት ሚያዚያ 4 ቀን 2018 ዓ.ም በጁባ ስታዲየም ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ በቤተልሔም ግዛቸው እና ምኀረት አየለ ጎሎች 2 ለ 0 አሸንፋለች። በራውዳ አሊ የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ወደ ቀጣዩ ዙር የማለፍ እድሉን አስፍቷል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከጁባ ከተመለሰ በኋላ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ዝግጅቱን ሲያደርግ መቆየቱንና ትናንት ደግሞ የመጨረሻ ልምምዱን ማከናወኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በሞሰስ ዛካሪያ ንጎር የሚሰለጥነው የደቡብ ሱዳን ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከትናንት በስቲያ አዲስ አበባ የገባ ሲሆን የመጨረሻ ልምምዱንም ትናንት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም አከናውኗል። ኢትዮጵያ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈች በሁለተኛው ዙር ከብሩንዲ ጋር ትጫወታለች። ትናንት በተደረገ የመልስ ጨዋታ ብሩንዲ ማላዊን 2 ለ 1 በማሸነፍ በአጠቃላይ ድምር ውጤት ተጋጣሚዋን 4 ለ 2 በመርታት ወደ ሁለተኛው ዙር አልፋለች። 10ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት ሴቶች የዓለም ዋንጫ በሞሮኮ አስተናጋጅነት ከጥቅምት 7 እስከ ጥቅምት 28 ቀን 2019 ዓ.ም ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። በማጣሪያ የሚያልፉ አራት የአፍሪካ ሀገራት በሶስት ዙሮች በሚደረጉ ጨዋታዎች ይለያሉ።
ማንችስተር ሲቲ ከአርሰናል ፦ የዋንጫው ዕጣ ፈንታ የሚወሰንበት ታላቅ ፍልሚያ
Apr 19, 2026 172
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ማንችስተር ሲቲ ከአርሰናል የሚያደርጉት ጨዋታ የዓለም እግር ኳስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። ጨዋታው ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ላይ በኢትሃድ ስታዲየም ይካሄዳል። ማንችስተር ሲቲ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ64 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አርሰናል በ70 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ሁለቱ ክለቦች በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሲገናኙ የአሁኑ ለ58ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም በነበራቸው 57 የሊግ ግንኙነት አርሰናል 25ቱን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ 19 ጊዜ ድል ሲቀናው በቀሪ 13 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በ57ቱ ጨዋታዎች አርሰናል 82 ግቦችን ሲያስቆጥር፣ ማንችስተር ሲቲ 75 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቡድኖቹ ባለፉት 10 የሊግ ግንኙነታቸው ሲቲ አምስት ጊዜ ሲያሸንፍ አርሰናል በሁለቱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርተዋል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት በአምስተኛ ሳምንት በኤምሬትስ ስታዲየም ባደረጉት የሊግ ጨዋታ አንድ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በ32ኛ ሳምንት አርሰናል በቦርንማዝውዝ 2 ለ 1 መሸነፉና ማንችስተር ሲቲ ቼልሲን 3 ለ 0 ማሸነፉ የዋንጫው ፉክክር ላይ ዳግም ነፍስ ዘርቷል። ባለሜዳው ማንችስተር ሲቲ የዛሬውን ጨዋታ ማሸነፍ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው ከአርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሶስት ዝቅ እንዲያደርግ ያስችለዋል። አርሰናል ድል ከቀናው ዋንጫ የማንሳት እድሉ የበለጠ ሰፊ ይሆናል። ይህ የማንችስተር ሲቲ እና የአርሰናል ግጥሚያ በብዙዎች ዘንድ 'የዘንድሮውን የፕሪሚየር ሊጉ ዋንጫ መዳረሻን የሚበይን' ታላቅ ፍልሚያ ተብሎ ተፈርጇል። የ47 ዓመቱ አንቶኒ ቴይለር ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች ጨዋታዎች ኤቨርተን ከሊቨርፑል ከቀኑ 10 ሰዓት በሂል ዲኪንሰን ስታዲየም የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ ይጠበቃል። አስቶንቪላ ከሰንደርላንድ እና ኖቲንግሃም ፎረስት ከበርንሌይ በተመሳሳይ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ሪያል ሶሲዬዳድ የኮፓ ዴል ሬይ ዋንጫን ለአራተኛ ጊዜ አነሳ
Apr 19, 2026 115
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በስፔን የኮፓ ዴል ሬይ የፍጻሜ ጨዋታ ሪያል ሶሲዬዳድ አትሌቲኮ ማድሪድን በመለያ ምት አሸንፏል። በሲቪያ ላ ካርቱጃ ስታዲየም በተካሄደው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በ90 ደቂቃ አትሌቲኮ ማድሪድ እና ሪያል ሶሲዬዳድ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። አዴሞላ ሉክማን እና ጁሊያን አልቫሬዝ ለአትሌቲኮ ማድሪድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አንደር ባሬኔትክሲያ በጨዋታ እና ማይክል ኦያርዛባል በፍጹም ቅጣት ምት ለሪያል ሶሲዬዳድ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ክለቦቹ አቻ በመለያየታቸው 30 ደቂቃ ተጨምሯል። በጭማሪ ሰዓት ግብ ባለመቆጠሩ ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቷል። ሪያል ሶሲዬዳድ በመለያ ምት 4 ለ 3 በማሸነፍ የስፔን ኮፓ ዴል ሬይን (የንጉሱ ዋንጫ) ለአራተኛ ጊዜ አንስቷል። የባስኩ ክለብ ከአምስት ዓመታት በኋላ የውድድሩ አሸንፏል። አትሌቲኮ ማድሪድ ከ13 ዓመታት በኋላ የኮፓ ዴል ሬይን ዋንጫ የማንሳት ህልሙ አልተሳካም። የማድሪዱ ክለብ 10 ጊዜ ውድድሩን አሸንፏል።
ማንችስተር ዩናይትድ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Apr 19, 2026 111
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ማንችስተር ዩናይትድ ቼልሲን 1 ለ 0 አሸንፏል። በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማትያስ ኩንሃ በ43ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ባለሜዳው ቼልሲ በርካታ የግብ እድሎችን ቢፈጥርም መጠቀም አልቻለም። በሁለት አጋማሽ የግብ ቋሚ እና አግጣሚ የገጨባቸው አጋጣሚዎች ተጠቃሽ ናቸው። ዩናይትድ በጨዋታው ያገኘውን ግልጽ የግብ እድል በመጠቀም አሸንፏል። በሊጉ 16ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ዩናይትድ በ58 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ዩናይትድ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመሳተፉ ነገር እውን ሊሆን ተቃርቧል። በውድድር ዓመቱ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቼልሲ በ48 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ተሸንፏል። የዛሬው ሽንፈት ቼልሲ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመሳተፍ እድሉን ይበልጥ የጠበበ አድርጎታል። በጨዋታው ለግቡ መቆጠር ምክንያት የሆነው ብሩኖ ፈርናንዴዝ በሊጉ ለ18ኛ ጊዜ ለጎል የሚሆን ኳስ አመቻችቶ አቀብሏል።
ወራጅ ቀጠና የሚገኘው ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከብራይተን ጋር አቻ ተለያየ
Apr 18, 2026 455
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 10 /2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ብራይተን ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በቶተንሃም ሆትስፐርስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፔድሮ ፖሮ እና ዣቪ ሲመንስ ጎሎቹን ለስፐርስ አስቆጥረዋል። ካሩ ሚቶማ እና ጆርጂኒዮ ሩተር ለብራይተን ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ባለሜዳው ቶተንሃም አሸነፈ ተብሎ ሲጠበቅ ጆርጂኒዮ ሩተር በ95ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠረው ጎል ብራይተንን አቻ አድርጓል። የቶተንሃሙ ተከላካይ ኬቨን ዳንሶ የሰራው ስህተት ለሩተር ጎል መቆጠር ምክንያት ሆኗል። የሩተር ጎል ለቶተንሃም ተጫዋቾች እና ደጋፊዎች ቅስም ሰባሪ ሆኗል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ31 ነጥብ ደረጃውን 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት 15 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ብራይተን በ47 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከወራጅ ቀጠና የወጣበት ወሳኝ ድል አስመዘገበ
Apr 18, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ነፃነት ገብረመድህን በ38ኛው እና ፍሬው ሰለሞን በ93ኛው ደቂቃ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ32 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ወደ 14ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ34 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ ቀን ላይ በተካሄደ የ28ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ ፋሲል ከነማን 3 ለ 0 አሸንፏል።
የዓለም አትሌቲክስ አዲስ አበባ የ2027ቱን የግራንድ ፕሪክስ ውድድር በወርቅ ደረጃ እንድታዘጋጅ ወሰነ
Apr 18, 2026 415
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ አዲስ አበባ የ2027ቱን የዓለም አትሌቲክስ የግራንድ ፕሪክስ ውድድር በወርቅ ደረጃ እንድታዘጋጅ ተመርጣለች። የዓለም አትሌቲክስ የአንድ ቀን ውድድር የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ ስታዲየም ዛሬ ተካሄዷል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ አጠቃላይ ዝግጅት፣ በመሰረተ ልማቱ ምቹነት፣ በውድድር ሂደቱ እና በደጋፊ የከተማችን ነዋሪ ሞራል እና ስፖርታዊ ጨዋነት በመደመም፤ አዲስ አበባ በሚቀጥለው ዓመት በፈረንጆቹ በ2027 የሚካሄደውን የግራንድ ፕሪክስ ውድድር በወርቅ ደረጃ እንድታዘጋጅ የዓለም አትሌቲክስ በዛሬው መርሐ ግብር ላይ ይፋ ማድረጉን ገልጸዋል። ከንቲባዋ ውድድሩ በወርቅ ደረጃ እንዲደረግ በመወሰኑ እንኳን ደስ አለን ብለዋል።
ሊድስ ዩናይትድ እና ቦርንማውዝ ድል ቀንቷቸዋል
Apr 18, 2026 104
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት ጨዋታዎች መካሄዳቸውን ቀጥለዋል። በኢላንድ ሮድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሊድስ ዩናይትድ ዎልቭስን 3 ለ 0 አሸንፏል። ኖሃ ኦካፎር እና ጀምስ ጀስቲን በጨዋታ፣ ዶምኒክ ካልቨርት-ሉዊን በፍጹም ቅጣት ምት ጎሎቹን አስቆጥረዋል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን ያስመዘገበው ሊድስ ዩናይትድ በ39 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ላለመውረድ በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 22ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ዎልቭስ በ17 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ዎልቭስ በ34ኛ ሳምንት በቶተንሃም ሆትስፐርስ ከተሸነፈ ከሊጉ መወረዱ ይረጋገጣል። በሌላኛው መርሐ ግብር ቦርንማውዝ ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 1 አሸንፏል። በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ማርከስ ታቫርኒየር እና አድሪያን ትሩፌርት የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሊጉ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው ቦርንማውዝ በ48 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት 13 የሊግ ጨዋታዎች አልተሸነፈም። በውድድር ዓመቱ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኒውካስትል ዩናይትድ በ42 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከብራይተን፣ ቼልሲ ከማንችስተር ዩናይትድ ምሽት አራት ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
ዛሬ ኢትዮጵያ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ የዓለም አትሌቲክስ የአንድ ቀን የሩጫ ውድድርን በአዲስ አበባ በድምቀት አስተናግዳለች - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 18, 2026 372
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ ዛሬ ኢትዮጵያ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ የዓለም አትሌቲክስ የአንድ ቀን የሩጫ ውድድርን በአዲስ አበባ በድምቀት ማስተናገዷን ከንቲባ አዳነች አበቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ይህ ስኬት በከተማችን የገነባናቸው ዘመናዊ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ውጤት ከመሆኑም ባለፈ፣ አገራችን በአትሌቲክስ ዘርፍ ያላትን ታላቅ ዝና ዳግም ያረጋገጠ ነው ብለዋል። በሚያዝያ ወር ብቻ የምናስተናግዳቸው ሦስት ታላላቅ ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ኩነቶች፣ ከተማችን ማንኛውንም ዓይነት ዓለም አቀፍ ውድድር የማስተናገድ ብቃትና ደረጃ ላይ መድረሷን የሚያሳዩ ናቸው ሲሉም ገልጸዋል። እነዚህ ውድድሮች ተተኪ አትሌቶችን ከማነቃቃታቸውም በላይ ለስፖርታዊ ቱሪዝም ዕድገት የጎላ ፋይዳ አላቸው። ይህ ታሪካዊ ውድድር በአዲስ አበባ መካሄዱ ከተማችንን ለነዋሪዎቿ ምቹና ሳቢ ከማድረግ ባለፈ፣ ለዓለም አቀፍ ኩነቶች ማራኪ የስበት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን በተግባር ያሳየ እውነት ነው ሲሉም ገልጸዋል። ውድድሩ በስኬት እንዲጠናቀቅ የተለመደውን ኢትዮጵያዊ ጨዋነትና እንግዳ ተቀባይነት ላሳዩት ስፖርት ወዳድ ነዋሪዎችም በራሴና በከተማ አስተዳደሩ ስም ላቅ ያለ ምስጋና አቅርበዋል። ለእንግዶቻችን በቆንጆዋ አዲስ አበባ የማይረሳና ያማረ ቆይታ እንዲሆንላችሁ እመኛለሁ ብለዋል ከንቲባ አዳነች አቤቤ ባስተላለፉት መልዕክት።
አዲስ አበባ ታሪካዊውን የአትሌቲክስ ውድድር በማዘጋጀቷ ክብር ይሰማናል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 18, 2026 120
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ አዲስ አበባ በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የዓለም አትሌቲክስ ውድድር በማዘጋጀቷ ክብር እና ኩራት ይሰማናል ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አበቤ የዓለም አዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአትሌቲክስ ውድድርን በይፋ አስጀምረዋል። ከንቲባዋ ንግግራቸው አዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ውድድር በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በማዘጋጀቷ ክብር ይሰማናል ሲሉ ተናግረዋል። አያይዘውም ውድድሩ በመዲናችን መካሄዱ ከተማችን የስህበት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን ያሳያል ብለዋል። ይህ ሁነት ከውድድር በተሻገረ መልኩ የመግባባት እና አብሮ የመቆም ተምሳሌት መሆኑን ከንቲባዋ አመልክተዋል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ በበኩላቸው፣ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ታላላቅ መድረኮችን በሀገራችን ማዘጋጀት መቻላችን መንግስት ለስፖርት የሰጠውን ትኩረት ያሳያል ብለዋል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ኮማንደር አትሌት ስለሺ ስህን በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ እንዲህ አይነት ታላቅ የውድድር መድረክ በማዘጋጀታችን እንደ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ብቻ ሳይሆን እንደ አትሌት ትልቅ ኩራት ተሰምቶኛል ሲሉ መግለጹን የፌዴሬሽኑ መረጃ ያመለክታል። በውድድሩ ይፋዊ የመክፈቻ ስነስርዓት ላይ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና፣ ማህበራዊ ልማት እና ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ ወርቅሰሙ ማሞ፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች፣ የኢትዮጵያ ታላላቅ አትሌቶች እና ከተለያዩ ሀገራት የተገኙ እንግዶች ታድመዋል።