ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ግብጽ ከቤልጂየም፤ ኬፕቨርዴ ከስፔን የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Jun 15, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ዛሬ አምስተኛ ቀኑን ይዟል። በምድብ ሰባት ቤልጂየም ከግብጽ በሲያትል ስታዲየም ምሽት አራት ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። አውሮፓዊቷ ሀገር ቤልጂየም በዓለም ዋንጫው ስትሳተፍ የአሁኑ ለ15ኛ ጊዜ ነው። ቤልጂየም በመድረኩ ትልቁ ውጤቷ እ.አ.አ በ2018 በሩሲያ በተካሄደው 21ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችበት ነው። ተጋጣሚዋ ግብጽ በዓለም ዋንጫ አራተኛ ተሳትፎዋን ታደርጋለች። የሰሜን አፍሪካዊቷ ሀገር በዓለም ዋንጫ ተሳትፎዋ ከምድብ አልፋ አታውቅም። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው አራት የወዳጅነት ጨዋታዎች ግብጽ ሶስት ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ስትይዝ ቤልጂየም አንድ ጊዜ ድል ቀንቷታል። የሀገራቱ ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። በምድብ ስምንት ምሽት አንድ ሰዓት ላይ ስፔን ከኬፕቨርዴ በአትላንታ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በዓለም ዋንጫው 17ተኛ ተሳትፎዋን የምታደርገው ስፔን እ.አ.አ በ2010 በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው 19ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ አሸናፊ በመሆን ብቸኛ ድሏን ማሳካት ችላለች። አፍሪካዊቷ የደሴት ሀገር ኬፕቨርዴ በዓለም ዋንጫው ስትሳተፍ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። በዚሁ በምድብ ስምንት ሳዑዲ አረቢያ ከኡራጓይ ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት ላይ በሚያሚ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሌላ በኩል በምድብ ሰባት ኢራን ከኒውዝላንድ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ በሎስ አንጀለስ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የ35ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን መርሐ ግብር
Jun 15, 2026 182
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 35ኛ ሳምንት አራት ጨዋታዎችን ዛሬ ይካሄዳሉ። ከቀኑ ሰባት ሰዓት ነገሌ አርሲ ከሃዋሳ ከተማ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ነገሌ አርሲ በ53 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ሃዋሳ ከተማ በ48 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ከድ የራቀው ነገሌ አርሲ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 የረታው ሃዋሳ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ በማለም ወደ ሜዳ ይገባል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሐ ግብር ሀዲያ ሆሳዕና ከፋሲል ከነማ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሀዲያ ሆሳዕና በ43 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ሲይዝ ፋሲል ከነማ በ46 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አቻ የወጣው ሀዲያ ሆሳዕና ወደ ድል መንገድ ለመመለስ ይፋለማል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሽንፈት ያስተናገደ ሲሆን ሶስት ለማግኘት ይጫወታል። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። አዳማ ከተማ በ39 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ45 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ካለፉት አምስት ሊግ ጨዋታዎች በአንዱ ብቻ ያሸነፈው አዳማ ከተማ ከወራጅ ቀጠና ስፍራ ፈቀቅ ለማለት ሶስት ነጥብ ማግኘት ግድ ይለዋል። በ34ኛ ሳምንት ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 ያሸነፈው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተከታታይ ድሉን ለማስመመዝገብ ይጫወታል። አርባምንጭ ከተማ ከምድረ ገነት ሽሬ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። አርባምንጭ ከተማ በ32 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ምድረ ገነት ሽሬ በ38 ነጥብ 17ኛ ደረጃን በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ34ኛ ሳምንት አርባምንጭ ከተማ መቻልን 2 ለ 1 ሲያሸንፍ ተጋጣሚው ምድረ ገነት ሽሬ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ጨዋታው በወራጅ ቀጠና ለሚገኙት ሁለቱ ቡድኖች እጅጉን ወሳኝ የሚባል ነው።
ኔዘርላንድስ እና ጃፓን አቻ ተለያዩ
Jun 15, 2026 180
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ መርሐ ግብር ኔዘርላንድስ እና ጃፓን ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በዳላስ ስታዲየም በተካሄደው የምድብ ስድስት የመጀመሪያ ጨዋታ ቨርጂል ቫን ዳይክ እና ክሬሴንሲዮ ሳመርቪል ለኔዘርላንድስ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኬቶ ናካሙራ እና ዳቺ ካማዳ የጃፓንን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የካማዳ የ88ኛ ደቂቃ ጎል ጃፓንን አቻ አድርጓል። አራቱም ግቦች የተቆጠሩበት ሁለተኛ አጋማሽ የተሻለ እንቅስቃሴ ተደርጎበታል። ሁለቱ ሀገራት በምድብ ስድስት የመጀመሪያ ነጥባቸውን አግኝተዋል። በዚሁ ምድብ ስዊድን ከቱኒዚያ ከሌሊቱ 11 ሰዓት በሞንትሬይ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በአለም ዋንጫው አፍሪካዊቷ ኮትዲቯር ድል ቀንቷታል
Jun 15, 2026 169
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ አምስት ሁለተኛ መርሐ ግብር ኮትዲቯር ኢኳዶርን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ከእኩለ ሌሊት በኋላ በፊላደልፊያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ተቀይሮ የገባው አማድ ዲያሎ በ90ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። አፍሪካዊቷ ኮትዲቯር በጨዋታው የተሻሉ የግብ እድሎችን ፈጥራለች። የኳስ ቁጥጥር ብልጫ የነበራት ኢኳዶር አንድ ኢላማውን የጠበቀ የግብ ሙከራ ብቻ አድርጋለች። ኮትዲቯር በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ድል ያስመዘገበች የመጀመሪዋ አፍካዊት ሀገር ሆናለች። በዓለም ዋንጫው በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ 10 የአፍሪካ ሀገራት እየተሳተፉ ይገኛል። በምድብ አምስት ትናንት በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ጀርመን ኩራሳኦን 7 ለ 1 አሸንፋለች። በቀጣይ ጀርመን ከኮትዲቯር የሚያደርጉት የምድብ ጨዋታ ይጠበቃል። ኢኳዶር ከኩራሳኦ ሌላኛው የምድቡ ሁለተኛ መርሐ ግብር ነው።
ስዊድን ቱኒዚያን 5 ለ 1 አሸንፋለች።
Jun 15, 2026 132
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ ስድስት ሁለተኛ ጨዋታ ስዊድን ቱኒዚያን 5 ለ 1 አሸንፋለች። ማለዳ ላይ በተጠናቀቀው እና በሞንቴሬይ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ያሲን አያሪ (ሁለት) ፣ አሌክሳንደር ኢሳቅ፣ ቪክቶር ዮኮሬሽ እና ማቲያስ ስቫንበርግ የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ኦማር ረኪክ የቱኒዚያን ግብ አስቆጥሯል። ቱኒዚያ በአንጻራዊነት የተሻለ የኳስ ቁጥጥር ቢኖራትም በበቂ ሁኔታ የግብ እድሎችን መፍጠር አልቻለችም። ስዊድን በርካታ የግብ እድሎችን ፈጥራለች። ውጤቱን ተከትሎ ስዊድን በሶስት ነጥብ ምድብ ስድስትን መምራት ጀምራለች። ቱኒዚያ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ ይዛለች። በዚሁ ምድብ ትናንት በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ኔዘርላንድስ እና ጃፓን ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ቱኒዚያ ከጃፓን፣ ስዊድን ከኔዘርላንድስ በምድብ ስድስት የሚደረጉ ቀጣይ መርሐ ግብሮች ናቸው።
በዓለም ዋንጫው ጀርመን በመጀመሪያ ጨዋታዋ ድል ቀንቷታል
Jun 14, 2026 592
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ አምስት የመጀመሪያ መርሐ ግብር ጀርመን ኩራሳኦን 7 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፋለች። ማምሻውን በሂውስተን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ካይ ሃቫርትዝ (ሁለት ጎሎች)፣ ፍሊክስ ንሜቻ፣ ኒኮ ሽሎተርቤክ፣ ጀማል ሙሲያላ፣ ናትናኤል ብራውን እና ዴኒዝ ኡንዳቭ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሊቫኖ ኮሜኔንሲያ የኩራሳኦ ብቸኛ ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ኮሜኔንሲያ ለመጀመሪያ ጊዜ በዓለም ዋንጫው ለተሳተፈችው ኩራሳኦ ግብ በማስቆጠር ታሪክ ሰርቷል። በጨዋታው ጀርመን ፍጹም የበላይነት ነበራት። ጨዋታው በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ከፍተኛ የግብ መጠን የተቆጠረበት ነው። ውጤቱን ተከትሎ የአራት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ጀርመን በሶስት ነጥብ ምድብ አምስትን መምራት ጀምራለች። ኩራሳኦ ያለ ምንም ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ምድብ ኮትዲቭዋር ከኢኳዶር ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት ላይ በፊላደልፊያ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የአፍሪካ አገራት ተሳትፎ በከፍተኛ ሁኔታ ያደገበት የዓለም ዋንጫ
Jun 14, 2026 261
አዲሱ የ48 ቡድኖች ተሳትፎ ከጠቀማቸው አህጉራት መካከል አፍሪካ አንዱ ነው። ቀደም ሲል ለአፍሪካ ይሰጥ የነበረው ቦታ አምስት ብቻ የነበረ ሲሆን፣ በዚኛው ውድድር ግን ዘጠኝ ሀገራት በቀጥታ የመሳተፍ እድል አግኝተዋል። በዚህም መሰረት ሞሮኮ፣ ሴኔጋል፣ ግብፅ፣ ኮትዲቯር፣ አልጄሪያ፣ ቱኒዚያ፣ ጋና፣ ኬፕቨርዴ እና ደቡብ አፍሪካ በቀጥታ ያለፉ የአፍሪካ ሀገራት ናቸው። በአንጻሩ የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ብሔራዊ ቡድን በክፍለ አህጉራዊ አህጉር አቋራጭ የማጣሪያ ውድድር (Play-off) የጃማይካን አቻውን በመርታት ለዓለም ዋንጫው ያለፈች 10ኛዋ የአፍሪካ ሀገር በመሆን አዲስ ታሪክ ሰርታለች።
በተጠባቂው ጨዋታ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 2 ለ 1 አሸንፏል
Jun 14, 2026 251
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 7 /2018 (ኢዜአ)፦ በተጠባቂው የ35ኛ ሳምንት ሲቢኢ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ ግብር ጨዋታ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 2 ለ 1 አሸንፏል፡ ቀን 9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 2 ለ 1 አሸንፏል፡፡ ለሲዳማ ቡና የማሸነፊያ ግቦቹን ያሬድ ባየህ እና ብርሃኑ በቀለ ሲያስቆጥሩ፥ ኢትዮጵያ ቡናን ከሽንፈት ያልታደገች ግብ ዘላለም አባተ ከመረብ አሳርፏል፡፡ በተመሳሳይ ሰዓት በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው የዕለቱ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ መቻልን 3 ለ 0 ሲያሸንፍ ፍፁም ጥላሁን፣ ሀብታሙ ጉልላት እና የአብስራ ጎሳዬ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል፡፡
የዓለም 73 በመቶ ህዝብ ይከታተለዋል ተብሎ የሚጠበቀው የዓለም ዋንጫ እውነታዎች
Jun 14, 2026 254
23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በአሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ ጣምራ አዘጋጅነት መካሄድ ከጀመረ ዛሬ አራተኛ ቀኑን አስቆጥሯል። የዘንድሮው የዓለም ዋንጫ “በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ” የሚያስብሉ ሁነቶች የሚያስተናገዱበት ውድድር እንደሚሆን እየተነገረ ይገኛል። የዘንድሮውን ዓለም ዋንጫው የተመለከቱ እውነታዎች እንደሚከተለው ቀርበዋል:- 1. በታሪክ ትልቁ የቡድኖች ቁጥር (48 ብሔራዊ ቡድኖች) ዓለም ዋንጫ ከተለመደው የ32 ቡድኖች የውድድር ፎርማት ወጥቶ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ 48 አገራት ይሳተፉበታል። 2. ታሪካዊ የሶስት አገራት ጥምር አስተናጋጅነት ይህ የዓለም ዋንጫ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በሶስት አገራት (በአሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ) በጋራ የሚዘጋጅ ይሆናል። ከዚህ ቀደም ከአንድ በላይ አገር ውድድሩን ያስተናገደው እ.አ.አ በ2002 ጃፓን እና ኮሪያ ሪፐብሊክ በጋራ ባሰናዱት 17ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ላይ ነው። 3. 104 ጨዋታዎች (በዓለም ዋንጫ ታሪክ ከፍተኛ የጨዋታዎች መጠን) በቡድኖች ቁጥር መጨመር ምክንያት በውድድሩ ላይ የሚደረጉት አጠቃላይ ጨዋታዎች ቁጥር ወደ 104 ጨዋታዎች ከፍ ብሏል። ይህም እ.አ.አ በ2022 በኳታር አስተናጋጅነት ከተካሄደው 22ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ላይ ከነበረው የ64 ጨዋታዎች ቁጥር በእጅጉ ጨምሯል። 4. አዲሱ የጥሎ ማለፍ ዙር ከዚህ ቀድሞ በነበሩ የዓለም ዋንጫ ውድድሮች በስምንት ምድቦች ሁለት ሁለት ቡድኖች ቀጥታ ወደ 16ቱ ዙር ከሚሄዱበት አሰራር ይተገበር ነበር። የ2026ቱ ውድድር 12 ምድቦች (እያንዳንዳቸው አራት ሀገራት) ይኖሩታል። ከእያንዳንዱ ምድብ አንደኛና ሁለተኛ የሚወጡት እንዲሁም ምርጥ ሶስተኛ ደረጃን የያዙ ስምንት ሀገራትን ጨምሮ ወደ አዲሱ የ32 ሀገራት ጥሎ ማለፍ የሚሸጋገሩ ይሆናል። ይህም የዓለም ዋንጫውን አንድ ተጨማሪ የጥሎ ማለፍ እርከን እንዲጨምር አድርጎታል። 5. የኤስታዲዮ አዝቴካ የሶስት ጊዜ ታሪካዊ ክብረወሰን በሜክሲኮ ሲቲ የሚገኘው ታዋቂው ኤስታዲዮ አዝቴካ ስታዲየም በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በሶስት የተለያዩ የዓለም ዋንጫዎች (1970፣ 1986 እና 2026) ጨዋታዎችን በማስተናገድ ቀዳሚው ሆኗል። ስታዲየሙ በሶስቱም ውድድሮች የመክፈቻ ጨዋታዎችን የመምራት ልዩ ክብረወሰንም አለው። 6. የ16ቱ አስተናጋጅ ከተሞች ስብጥር የዓለም ዋንጫ ጨዋታዎች በሰሜን አሜሪካ በሚገኙ 16 ከተሞች ላይ ይካሄዳሉ። አሜሪካ ከፍተኛውን ድርሻ በመውሰድ 11 ከተሞችን ስታቀርብ፣ ሜክሲኮ ሶስት፣ ካናዳ ደግሞ ሁለት ከተሞችን አዘጋጅተዋል፡ • አሜሪካ: አትላንታ፣ ቦስተን፣ ዳላስ፣ ሂውስተን፣ ካንሳስ ሲቲ፣ ሎስ አንጀለስ፣ ማያሚ፣ ኒው ዮርክ/ኒው ጀርሲ፣ ፊላደልፊያ፣ ሳን ፍራንሲስኮ፣ ሲያትል። • ሜክሲኮ: ጓድላሀራ፣ ሜክሲኮ ሲቲ፣ ሞንቴሬይ። • ካናዳ: ቶሮንቶ እና ቫንኩቨር። 7. የፍፃሜው ጨዋታ ስታዲየም በጉጉት የሚጠበቀው የዓለም ዋንጫ ፍፃሜ ጨዋታ በኒው ጀርሲ (ኤዘርፎርድ) በሚገኘውና በውድድሩ ወቅት "ኒው ዮርክ ኒው ጀርሲ ስታዲየም" ተብሎ በሚጠራው ሜትላይፍ ስታዲየም (MetLife Stadium) ይደረጋል። ስታዲየሙ ወደ 82,500 የሚጠጉ ተመልካቾችን የመያዝ ግዙፍ አቅም አለው። 8. የአፍሪካ አገራት ተሳትፎ በከፍተኛ ሁኔታ ያደገበት የዓለም ዋንጫ አዲሱ የ48 ቡድኖች ተሳትፎ ከጠቀማቸው አህጉራት መካከል አፍሪካ ነው። ቀደም ሲል ለአፍሪካ ይሰጥ የነበረው ቦታ አምስት ብቻ የነበረ ሲሆን፣ በዚኛው ውድድር ግን ዘጠኝ ሀገራት በቀጥታ የመሳተፍ እድል አግኝተዋል። በዚህም መሰረት ሞሮኮ፣ ሴኔጋል፣ ግብፅ፣ ኮትዲቯር፣ አልጄሪያ፣ ቱኒዚያ፣ ጋና፣ ኬፕቨርዴ እና ደቡብ አፍሪካ በቀጥታ ያለፉ የአፍሪካ ሀገራት ናቸው። በአንጻሩ የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ብሔራዊ ቡድን በክፍለ አህጉራዊ አህጉር አቋራጭ የማጣሪያ ውድድር (Play-off) የጃማይካን አቻውን በመርታት ለዓለም ዋንጫው ያለፈች 10ኛዋ የአፍሪካ ሀገር በመሆን አዲስ ታሪክ ሰርታለች። 9. ታሪክ ሰሪ አገራት የ48 ቡድኖች ተሳትፎ ለአገራት አዲስ ዕድል ፈጥሯል። በዚህ ውድድር ላይ የደሴቲቷ ሀገር ኩራሳኦ (156 ሺህ ገደማ ህዝብ አላት) ለዓለም ዋንጫ ያለፈች ትንሽ አገር በመሆን ታሪክ ሰርታለች። ኬፕቨርዴ (ከአፍሪካ)፣ ኡዝቤኪስታን እና ጆርዳንም ለመጀመሪያ ጊዜ በዓለም ዋንጫ መድረክ ላይ ይሳተፋሉ። 10. በታሪክ ትልቁ የገንዘብ ሽልማት (871 ሚሊዮን ዶላር) ፊፋ አጠቃላይ የፋይናንስ ማከፋፈያ ፓኬጁን ወደ ታሪካዊው 871 ሚሊዮን ዶላር አሳድጎታል። ይህም የ655 ሚሊዮን ዶላር ቀጥተኛ የስፖርት ሽልማትን ጨምሮ የዝግጅትና የልዑካን ድጎማዎችን ያጠቃልላል። በዚህም መሰረት ማንኛውም ማጣሪያውን አልፎ የተሳተፈ አገር ለምድብ ጨዋታው ብቻ 12.5 ሚሊዮን ዶላር የሚያገኝ ሲሆን፣ አሸናፊው አገር ደግሞ የ50 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ያገኛል። 11. ግዙፉ የተፈጥሮ ሳር (Natural Grass) ሽግግር ፕሮጀክት ፊፋ የዓለም ዋንጫ ጨዋታዎች በተፈጥሮ ሳር ላይ ብቻ መደረግ አለባቸው የሚል ጥብቅ ህግ ስላለው፣ እንደ ዳላስ፣ ኒው ጀርሲ እና አትላንታ ያሉ በርካታ ሰው ሰራሽ ሳር (Artificial Turf) የሚጠቀሙ ስታዲየሞች ግዙፍ የምህንድስና ስራ አከናውነዋል። ለዚህም ሲባል በሚሊዮኖች የሚቆጠር ዶላር የወጣበትና በልዩ ሁኔታ በፕላስቲክ ንጣፎች ላይ የለማ የተፈጥሮ ሳር ወደ ስታዲየሞቹ የገባ ሲሆን፣ ሳሩ እንዳይደርቅ ጊዜያዊ የውሃ ማፍሰሻ፣ የንፋስ መናፈሻና “LED” የተሰኘ የመብራትና የብርሃን ስርዓት ተገጥሞላቸዋል። 12. የበረኞች የሰዓት ማባከን አዲስ የቅጣት እርምጃ የጨዋታውን ፍሰት መጠን መጠን ለማሳደግና ሆን ተብሎ የሚደረግን የሰዓት ማባከን ለመግታት የዓለም አቀፉ እግር ኳስ ማህበር ቦርድ (IFAB) እና ፊፋ ባስተላለፉት አዲስ ጥብቅ መመሪያ መሰረት፣ አንድ ግብ ጠባቂ ኳስ በእጁ ይዞ መቆየት የሚችለው ለስምንት ሴኮንዶች ብቻ ሲሆን፣ ዋናው ዳኛም የመጀመሪያዎቹ ሶስት ሴከንዶች ካለፉ በኋላ የቀሩትን የመጨረሻዎች አምስት ሴከንዶች በእጁ ጣቶች ወደ ላይ በማሳየት በግልጽ መቁጠር ይጀምራል። ግብ ጠባቂው ከተፈቀደው ከዚህ የስምንት ሴኮንድ ገደብ በላይ ኳሱን አዘግይቶ ከተገኘም ዳኛው ቀድሞ በሳጥን ውስጥ ይሰጥ የነበረውን ቀጥተኛ ያልሆነ የቅጣት ምት (Indirect Free Kick) ሙሉ በሙሉ በመሰረዝ ወዲያውኑ ለተቃራኒ ቡድን የማዕዘን ምት (Corner Kick) የሚሰጥ ሲሆን፣ ድርጊቱን በድጋሚ በሚፈጽሙ በረኞች ላይም የቢጫ ካርድ ማስጠንቀቂያ የመስጠት ሙሉ ስልጣን ተሰጥቷቸዋል። 14. ሶስቱ አስተናጋጅ አገራት በቀጥታ ያለፉበት የመጀመሪያው የዓለም ዋንጫ አንድ አስተናጋጅ አገር በቀጥታ የማለፍ መብት ማግኘቱ የተለመደ ቢሆንም፣ የ2026ቱ ውድድር ግን ሶስት አስተናጋጅ አገራት (አሜሪካ፣ ሜክሲኮ እና ካናዳ) በቀጥታ ያለፉበት የመጀመሪያው ዓለም ዋንጫ ነው። 15. የ1 ሺህ 248 ተጫዋቾች ግዙፍ ሎጂስቲክስ የቡድኖች ቁጥር ወደ 48 ማደጉ (እያንዳንዱ ቡድን 26 ተጫዋቾችን ይዞ ስለሚመጣ) በአጠቃላይ 1 ሺህ 248 ተጫዋቾች በውድድሩ ላይ ይሳተፋሉ። ይህን ግዙፍ ቁጥር ለማስተናገድ ፊፋ በስፖርት ታሪክ ትልቁን የጸጥታ፣ የቤትና የልምምድ ሜዳ ዝግጅት አጠናቋል። በተጨማሪም ቡድኖቹ በጨዋታዎች መካከል ሙሉ ትኩረታቸውን እንዲሰበስቡ በመላው አህጉሪቱ ከ40 በላይ ኦፊሴላዊ የካምፕ ማዕከላትን አዘጋጅቷል። 16. ስድስት ቢሊዮን ህዝብ (ከዓለም ህዝብ 73 በመቶ ) ፊፋ እና የዓለም አቀፍ የሚዲያ ተንታኞች ባወጡት መረጃ መሰረት፣ የዘንድሮውን የዓለም ዋንጫ በዓለም ዙሪያ 6 ቢሊዮን ገደማ ህዝብ በተለያዩ የመገናኛ ዘዴዎች ይከታተለዋል። ይህም በአሁኑ ወቅት ካለው አጠቃላይ የዓለም ህዝብ ቁጥር ወደ 73 በመቶ የሚሆነው ውድድሩን ይከታተለዋል ማለት ነው። ይህም እ.አ.አ 2022 በኳታር በተካሄደው 22ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የአምስት ቢሊዮን ተመልካች ቁጥር በእጅጉ የላቀ ያደርገዋል። የ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ፍጻሜ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ በርካታ ዜጎች ይከታተሉታል ተብሎ ይጠበቃል። የዓለም ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታ ላይ ብቻ ከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን በላይ ተመልካች በቀጥታ ስርጭት ስክሪኖች ይከታተለዋል ተብሎ ይጠበቃል። በቴሌቪዥን መስኮት ከሚያየው በቢሊዮን የሚቆጠር ህዝብ በተጨማሪ፣ በሶስቱ አስተናጋጅ አገራት በሚገኙት ግዙፍ ስታዲየሞች ውስጥ በመግባት ጨዋታዎቹን በአካል በቀጥታ የሚከታተሉ ደጋፊዎች ቁጥር ከአምስት ሚሊዮን በላይ እንደሚሆን ፊፋ አረጋግጧል። ከ500 ሚሊዮን በላይ ተመልካች የትኬት ግዢ ጥያቄ መቅረቡ የፍላጎቱን ከፍተኛነት ያሳያል። 17. የጂኦግራፊ ርቀትና የጉዞ ፈተና ውድድሩ ከካናዳዋ ቫንኩቨር እስከ ሜክሲኮ ሲቲ ድረስ በሺዎች የሚቆጠሩ ማይሎችን ስለሚሸፍን፣ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) የተጫዋቾችንና የደጋፊዎችን የረጅም ሰዓት በረራ ድካም ለመቀነስ ሲል አስተናጋጅ ከተሞቹን በሶስት ቀጣናዊ ዞኖች (ምዕራብ፣ መካከለኛው እና ምስራቅ) ከፍሎታል። ይህ የአህጉሪቱ ግዙፍ ስፋት በቡድኖች አዘገጃጀት ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ ከፍተኛ በመሆኑ፣ ፊፋ በምድብ ጨዋታዎች ወቅት አንድ ቡድን ከአንድ ቀጣና ወደ ሌላ ቀጣና ተሻግሮ እንዳይጫወት የጉዞ ገደብ ጥሏል። በዚህም ምክንያት ቡድኖችና ደጋፊዎች በአንድ ቀጣና ውስጥ ብቻ ስለሚመላለሱ የሚጠብቃቸው የበረራ ርቀት በእጅጉ የሚቀንስ ሲሆን፣ ከዚህ በተጨማሪም ተጫዋቾች በተለያዩ የአሜሪካ ከተሞች መካከል ያለውን ፍጹም የተለያየ የሰዓት አቆጣጠር ልዩነት በፍጥነት እንዲላመዱ እና በምስራቅና ምዕራብ የባህር ዳርቻዎች መካከል የሚፈጠረውን የሰውነት የጉዞ ድካም ለመከላከል ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ተገልጿል። 18. የካርቦን ልቀትን ለመቀነስ የተነደፈው የ”አረንጓዴ የጉዞ" ዕቅድ በሶስት ግዙፍ አገራት መካከል የሚደረገው ጉዞ ከፍተኛ የአውሮፕላን በረራዎችን ስለሚጠይቅ፣ ፊፋ የአየር ብክለትን እና የካርቦን ልቀትን (Carbon Footprint) ለመቀነስ አዲስ የጨዋታ አደረጃጀት ዘርግቷል። ቡድኖች በምድብ ጨዋታ ወቅት በአንድ ቀጠና ውስጥ እንዲቆዩ ከመደረጉም በላይ፣ ደጋፊዎች በከተሞች መካከል በሚጓዙበት ወቅት ከአውሮፕላን ይልቅ ባቡሮችን እና የኤሌክትሪክ የህዝብ ማመላለሻዎችን እንዲጠቀሙ የሚያበረታታ ልዩ የአረንጓዴ ትራንስፖርት ትስስር ተፈጥሯል። 19. የተጫዋቾችን ደህንነት ለመጠበቅ የመጣው የጭንቅላት ጉዳት (Concussion) ህግ ፊፋ ለተጫዋቾች ጤና እና ደህንነት ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት፣ በዚህ የዓለም ዋንጫ ላይ አዲስ የሕክምና መመሪያን በይፋ ተግባራዊ አድርጓል። በጨዋታ ላይ ሁለት ተጫዋቾች በራሳቸው ተጋጭተው አንደኛው በከባድ የጭንቅላት መቀጥቀጥ አደጋ ከተጎዳ፣ ቡድኑ የተፈቀደለትን የአምስት ተጫዋቾች ቅያሬ ጨርሶ እንኳ ቢሆን፣ የሕክምና ቡድኑን ፍቃድ በመውሰድ ተጨማሪ ስድስተኛ ተጫዋች የመቀየር (Permanent Concussion Sub) እንዲችል ሕጉ ፈቅዶለታል። ይህ አሰራር ተጫዋቾች ለጉዳት ሳይዳረጉ ጤናቸው ተጠብቆ እንዲጫወቱ ትልቅ ዋስትና ሆኗል። 20. በኳስ ታሪክ ረጅሙን ርቀት የሚጓዘው የዓለም ዋንጫ ችቦ (Trophy Tour) ይህ ታሪካዊ ውድድር በአንድ አገር ድንበር ብቻ የሚገደብ ባለመሆኑ፣ በታዋቂ የዓለም ዋንጫ ስፖንሰሮችንና በታዋቂ ሰዎች ታጅቦ የሚደረገው ይፋዊ የጉብኝት መርሃ ግብር (FIFA World Cup Trophy Tour) በስፖርቱ ታሪክ እጅግ ረጅሙ እና ሰፊው ሆኖ ተመዝግቧል። ዋንጫው በሦስቱ አስተናጋጅ አገራት (አሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ) ውስጥ የሚገኙትን 16ቱንም አስተናጋጅ ከተሞች ጨምሮ፣ ከ150 በላይ የዓለም አገራትን የሚያካልል ሲሆን፣ ይህም በሚሊዮን የሚቆጠሩ ደጋፊዎች ታሪካዊውን ዋንጫ በአቅራቢያቸው ሆነው በአካል እንዲያዩና የውድድሩ ስሜት ከመጀመሩ በፊት በመላው ዓለም እንዲቀጣጠል አስችሏል። እ.አ.አ ሴፕቴምበር 2025 የተጀመረው ጉዞ ከዘጠኝ ወራት በኋላ ተጠናቆ በሜክሲኮ እና ደቡብ አፍሪካ የመክፈቻ ጨዋታ ባስተናገደው ታሪካዊው አዜቴክ ስታዲየም አድርጓል።
ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት ስፖርታዊ ውድድሮችን የማስፋትና ዘርፉን በእውቀት የመምራት ጥረቶች ይጠናከራሉ
Jun 14, 2026 244
ባህር ዳር፤ ሰኔ 7/2018 (ኢዜአ)፦ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት ስፖርታዊ ውድድሮችን የማስፋትና ዘርፉን በእውቀት የመምራት ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኮማንደር ስለሺ ስህን ገለጸ። 1ኛው የኢትዮጵያ 10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድር፣ ዛሬ በባህር ዳር ከተማ ተካሄዷል። በወቅቱም ኮማንደር ስለሺ ስህን እንደገለጸው፤ በኢትዮጵያ ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት የአትሌቲክስ ስፖርቱን በእውቀትና በአሰራር ማዕቀፍ ለማዘመን እየተሰራ ነው። የአትሌቲክስ ውድድሮችን በማዘጋጀት ተተኪ አትሌቶችን ለመመልመልና ታዋቂ አትሌቶች ደግሞ አቋማቸውን እንዲፈትሹ እየተደረገ መሆኑንም አንስተዋል። በዚህም የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድሮችን በዘላቂነት በማጠናከር ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ያላትን የበላይነት ማስቀጠል ላይ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። በባህር ዳር ከተማ በተካሄደው የጎዳና ላይ ሩጫ በዓለም አቀፍ መድረክ የሚሳተፉ ታዋቂ አትሌቶችን ጨምሮ ከ120 በላይ ወንድና ሴት አትሌቶች የተሳተፉበትና 10 ኪሎ ሜትርን የሸፈነ ውድድር መካሄዱን ጠቁመዋል። በቀጣይ የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድርን በማስፋት በርካታ የአትሌቲክስ ክለቦች እንዲያሳተፉ እንደሚደረግም አስረድተዋል። የአማራ ክልል ባህል፣ ስፖርትና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ መልካሙ ጸጋዬ በበኩላቸው፥ ባህር ዳርን ጨምሮ በክልሉ ከተሞች እየተገነቡ ያሉ የኮሪደርና ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ለሩጫ ውድድሩ ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውን ተናግረዋል። የባህርዳር ከተማ በቅርቡ ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ የሚመረቀውን የባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲዮም ገንብታ ለስፖርት ዘርፉ ዕድገት እየሰራች መሆኗን ጠቁመው የኮሪደር ልማቷም ለዛሬው ሩጫ ውድድር የተመቸ ድባብን ፈጥሯል ብለዋል። ይህንን ዘመናዊ የስፖርት መሰረተ ልማት በመጠቀምም ክልሉን በስፖርት ኢንቨስትመንት ተመራጭና ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል። የ10 ኪ/ሜ የጎዳና ላይ ሩጫ ውድድሩን በአሸናፊነት ያጠናቀቀው የአማራ ማረሚያ ቤቶች አትሌት ጀማል ይመር እንደገለጸው፣ ውድድሩ ለብቃት መለኪያና ለተተኪዎች ትልቅ መድረክ በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብሏል። ሌሎች ተመሳሳይ ውድድሮችን በሌሎች ክልሎች በሚገኙ ከተሞች በማዘጋጀትና የውድድር መድረክ በመፍጠር የአትሌቲክስ ስፖርትን ለማሳደግ መስራት እንደሚገባም አመልክቷል። ውድድሩ ስፖርታዊ አቋሟን ለመፈተሽ እንዳገዛት የገለጸችው ደግሞ በሴቶች 1ኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ክለብ ሯጯ አትሌት ውዴ ከፍያለው ናት። በመርሃ ግብሩ ላይም የፌዴራልና የክልል የዘርፉ አመራሮች የተገኙ ሲሆን፣ ለአሸናፊ አትሌቶችም የሜዳሊያና የገንዘብ ሽልማት ተበርክቷል።
በዓለም ዋንጫው ኮትዲቯር ከኢኳዶር ቱኒዚያ ከስዊድን የመጀመሪያ የዓለም ዋንጫ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ
Jun 14, 2026 164
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7 /2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የምድብ አምስት መርሐ ግብር ኮትዲቯር ከኢኳዶር ጋር ዛሬ ጨዋታዋን ታከናውናለች። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት ላይ በፊላደልፊያ ስታዲየም ይካሄዳል። ሁለቱ ሀገራት እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ኮትዲቯር በዓለም ዋንጫው ስትሳተፍ ለአራተኛ ጊዜ መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ። ተጋጣሚዋ ኢኳዶር ለአምስተኛ ጊዜ በውድድሩ ላይ ተሳትፎ ታደርጋለች። የምዕራብ አፍሪካዊቷ ሀገር ከዚህ ቀደም በዓለም ዋንጫ ተሳትፎዋ ባደረገቻቸው ዘጠኝ ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዳለች። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይታለች። በተሳትፎዋ ታሪክ ከምድቧ አልፋ አታውቅም። ኢኳዶር በዓለም ዋንጫው እስከ አሁን 13 ጨዋታዎችን አከናውና በአምስቱ ድል ሲቀናት በስድስት ጨዋታዎች ሽንፈትን ቀምሳለች። በተቀሩት ሁለት ጨዋታዎች አቻ ወጥታለች። ኢኳዶር እ.አ.አ በ2006 በጀርመን በተካሄደው 18ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ ደርሶ በእንግሊዝ 1 ለ 0 የተሸነፈችበት አጋጣሚ በውድድሩ ላይ ያስመዘገበችው ትልቁ ውጤቷ ነው። ኮትዲቯር እና ኢኳዶር የሚያደርጉት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በዚሁ ምድብ አምስት ጀርመን ከኩራሳኦ ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ በሂውስተን ስታዲየም ይጫወታሉ። የአራት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ እና ለ21ኛ ጊዜ በውድድሩ ላይ የምትሳተፈው ጀርመን ጨዋታውን የማሸነፍ ሰፊ ግምት አግኝታለች። 156 ሺህ ህዝብ ገደማ ያላት የደሴቲቷ ሀገር ኩራሳኦ ለመጀመሪያ ጊዜ በዓለም ዋንጫ የምታደርገው ተሳትፎ ትኩረት የሳበ ሲሆን ዜጎቿም ጨዋታውን በጉጉት ይጠብቁታል። በተያያዘም በዓለም ዋንጫ በምድብ ስድስት ቱኒዚያ ከስዊድን ጋር ከሌሊቱ 11 ሰዓት ላይ በሞንትሬይ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም አራት ጊዜ በወዳጅነት ጨዋታዎች ተገናኝተው ስዊድን ሁለት ጊዜ ስታሸንፍ ቱኒዚያ አንድ ጊዜ ድል ቀንቷታል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። የሰሜን አፍሪካዊቷ ሀገር ቱኒዚያ በዓለም ዋንጫው ስትሳተፍ የአሁኑ ለሰባተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም በነበራት ተሳትፎዎቿ ከምድቧ አልፋ አታውቅም። ስዊድን ለ14ኛ ጊዜ በዓለም ዋንጫው ላይ ትሳተፋለች። ትልቋ ውጤቷ ራሷ እ.አ.አ በ1958 ባዘጋጀችው ስድስተኛው የዓለም ዋንጫ በፍጻሜው በብራዚል 5 ለ 2 ተሸንፋ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችበት ነው። በምድብ ስድስት ሌላኛው መርሐ ግብር ኔዘርላንድስ ከጃፓን ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በዳላስ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የአዲስ አበባ የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ ልማት ስኬት ታዳጊዎች ስፖርታዊ ክህሎታቸውን የሚያሳድጉበት መሰረት ጥሏል
Jun 14, 2026 198
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ ልማት ስኬት ታዳጊዎች ስፖርታዊ ክህሎታቸውን የሚያሳድጉበት መሰረት መጣሉን የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ አስታወቀ። በመዲናዋ የተገነቡ ማራኪ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክቶች በርካታ የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ ልማቶች እንዲገነቡ አስችሏል። የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ ልማቶቹም የመዲናዋን ወጣቶች ስብዕና በመገንባት ስፖርታዊ ክህሎታቸውን የሚያበለፅጉበትን አስቻይ ምኅዳር ፈጥሯል። ይህም የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ ልማት እጥረትን በመቅረፍ በሁሉም የስፖርት ዘርፍ ብቃት ያላቸው ወጣት ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ምቹ መደላድል እየፈጠረ ይገኛል። የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የመዲናዋ የልማት ስኬቶች ለስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታ ምቹ መደላድልን መፍጠሩን ገልጸዋል። አዲስ አበባን የማስዋብ የልማት ውጤቶችም ብቁና ተወዳዳሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ውጤታማ የስፖርት ማዕከላትና ማዘውተሪያ ስፍራዎች እንዲገነቡ ማስቻሉን ተናግረዋል። በዚህም በሀገራዊ ለውጡ ማግስት ብቃትና ጥራት ያላቸው ታዳጊ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ 2 ሺህ 581 የስፖርት ማዘውተሪያና ማሰልጠኛ ማዕከላት መገንባታቸውን አስታውቀዋል። የስፖርት ማዘውተሪያ ስፋራና ማዕከላት ግንባታም በትምህርት ቤቶች፣ ቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛና ጤና ተቋማት ጨምሮም በመኖሪያ መንደሮች ላይ አካታች የስፖርት መሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን አስረድተዋል። የመዲናዋ የስፖርት ማዘውተሪያና ማሰልጠኛ ማዕከላቱም ተተኪ ስፖርተኞችን ከማፍራት ባሻገር ዘርፈ ብዙ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያስገኙ መሆኑን አንስተዋል። በበጎ ሥነ-ምግባር የታነጸ ዜጋን በማፍራትም ወጣቶችና ታዳጊዎች ጊዜያቸውን ከአልባሌ ስፍራ ማራቅ ያስቻለ ምኅዳር መፍጠሩን ጠቅሰዋል። የአዲስ አበባ ዘመናዊና ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ማዘውተሪያዎችም ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን የምታስተናግድበት አቅም የፈጠሩ መሆናቸውንም አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅትም በስፖርት ማዘውተሪያና ማሰልጠኛ ማዕከላት የሰለጠኑ ታዳጊዎች ወደተለያዩ ክለቦችና ብሔራዊ ቡድን ከፍተኛ የስፖርት ደረጃ እየተሸጋገሩ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ይህም በኢትዮጵያ የስፖርት ልማት ላይ ከፍተኛ ጠቀሜታ በማበርከት ታዳጊዎች ስፖርታዊ ክህሎታቸውን የሚያሳድጉበት መሰረት መጣሉን እንደሚያሳይ ተናግረዋል። በቀጣይም ተተኪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ የስፖርት ማዘውተሪያና ማሰልጠኛ ማዕከላት የመሰረተ ልማት ግንባታ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
አውስትራሊያ የዓለም ዋንጫውን በድል ጀምራለች
Jun 14, 2026 181
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ አውስትራሊያ ቱርኪዬን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ዛሬ ማለዳ በቢሲ ፕሌስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኔስትሮይ ኢራንኩንዳ በ27ኛው እና ኮነር ሜትካልፍ በ75ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። አውስትራሊያ በጨዋታው ብልጫ ቢወሰድባትም ያገኘቻቸውን የግብ እድሎች በሚገባ መጠቀሟ አሸናፊ አድርጋለች። ቱርኪዬ በጨዋታው ላይ የወሰደችውን ወደ ጎል መቀየር ተስኗቷል። ውጤቱን ተከትሎ አውስትራሊያ በምድብ አራት በሶስት ነጥብ ተመሳሳይ ነጥብ ባላት አሜሪካ በግብ ክፍያ ተበልጣ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። ከትናንት በስቲያ በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር አሜሪካ ፓራጓይን 4 ለ 1 ማሸነፏ የሚታወስ ነው። የምድባቸውን የመጀመሪያ ጨዋታ ያሸነፉት አሜሪካ እና አውስትራሊያ በቀጣይ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። ቱርኪዬ ከፓራጓይ ሌላኛው የምድብ ሁለተኛ ጨዋታ ነው።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ ቡና ጋር ወሳኝ ጨዋታ ያደርጋል
Jun 14, 2026 192
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2018 (ኢዜአ)፦ ከኢትዮጵያና ማላዊ የወዳጅነት ጨዋታዎች መልስ፣ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ በ35ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ይመለሳል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ ቡና ከሲዳማ ቡና በአዲስ አባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ቡና በ46 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ሲዳማ ቡና በ61 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። በ34ኛ ሳምንት በሃዋሳ ከተማ 1 ለ 0 የተሸነፈው ኢትዮጵያ ቡና ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በአንጻሩ ሲዳማ ቡና ካሸነፈ ለመጀመሪያ ጊዜ የሊጉን ዋንጫ ለማንሳት ይበልጥ ይቃረባል። ተከታዩ መቻል በቅዱስ ጊዮርጊስ ከተሸነፈ ሶስት ጨዋታዎች እየቀሩ የሊጉን ዋንጫ ማንሳቱን ያረጋግጣል። የቅዱስ ጊዮርጊስ እና መቻል ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ46 ነጥብ ስምትኛ ደረጃን ይዟል። መቻል በ53 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ያሸነፈው ቅዱስ ጊዮርጊስ በድል ጉዞው ለመቀጠል ይፋለማል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ያላገኘው መቻል በዋንጫ ፉክክሩ ላይ ለመቆየት ሶስት ነጥብ ማግኘት ይኖርበታል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ መድን ከድሬዳዋ ከተማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ43 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት የሊጉ ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። ድሬዳዋ ከተማ በ35 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ስምንት የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 35ኛ ሳምንት መርሐ ግብር እስከ ሰኔ 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው በ14 ጎሎች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ ናትናኤል ዳንኤል በ13 ግቦች ይከተላል።
ስኮትላንድ ድል ቀንቷታል
Jun 14, 2026 164
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ ሶስት ሁለተኛ መርሐ ግብር ስኮትላንድ ሀይቲን 1 ለ 0 አሸንፋለች። በቦስተን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆን ማጊን በ29ኛው ደቂቃ ጎሉን አስቆጥሯል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ግብ ያስቆጠረው ማጊን የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ ስኮትላንድ ምድብ ሶስትን በሶስት ነጥብ መምራት ጀምራለች። በዚህ ምድብ ትናንት በተደረገው ጨዋታ ብራዚል እና ሞሮኮ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሞሮኮ ከስኮትላንድ፣ ብራዚል ከሀይቲ በቀጣይ በምድቡ የሚደረጉ ሁለተኛ ጨዋታዎች ናቸው።
በተጠባቂው የዓለም ዋንጫ ጨዋታ ብራዚል እና ሞሮኮ አቻ ተለያዩ
Jun 14, 2026 468
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የምድብ ሶስት ተጠባቂ መርሐ ግብር ብራዚል እና ሞሮኮ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ከእኩለ ሌሊት በኋላ በኒው ዮርክ ኒው ጀርዚ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ እስማኤል ሳይባሪ በ21ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ሞሮኮ መሪ ሆናለች። ቪኒሸስ ጁኒየር በ32ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ግብ ብራዚልን አቻ አድርጓል። በጨዋታው ሞሮኮ ማራኪ እና ፍሰት ያለው የጨዋታ እንቅስቃሴ አድርጋለች። ብራዚል በክንፍ መስመር ተጫዋቾቿ ላይ የተመሰረተ የማጥቃት እንቅስቃሴ ስታደርግ ለመመልከት ተችሏል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ታይቶበታል። ሁለቱ ሀገራት በምድቡ የመጀመሪያ ነጥባቸውን አግኝተዋል። ሞሮኮ ከስኮትላንድ፣ ብራዚል ከሀይቲ ቀጣይ የምድብ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በምድብ ሶስት ሌላኛው መርሐ ግብር ሀይቲ ከስኮትላንድ ከሌሊቱ 10 ሰዓት በቦስተን ስታዲየም ይጫወታሉ።
ስዊዘርላንድ እና ኳታር አቻ ተለያዩ
Jun 13, 2026 378
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የምድብ ሁለት መርሐ ግብር ስዊዘርላንድ እና ኳታር ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። ማምሻውን በሳንፍራንሲስኮ ቤይ ኤሪያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብሬል ኢምቦሎ በ17ኛው በፍጹም ቅጣት ምት ጎሉን ከመረብ ላይ ባሳረፈው ጎል ስዊዘርላንድ መሪ ሆናለች። ይህም በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ በፍጹም ቅጣት ምት የተቆጠረ የመጀመሪያ ግብ ሆኗል። ቦዓለም ኩኪ በ95ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል ለኳታር ወሳኝ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። በጨዋታው ስዊዘርላንድ ብልጫ የወሰደች ቢሆንም ያገኘቻቸውን የግብ እድሎች በሚገባ መጠቀም አልቻለችም። ውጤቱን ተከትሎ ስዊዘርላንድ እና ኳታር በውድድሩ የመጀመሪያ ነጥባቸውን አግኝተዋል። በዚሁ ምድብ ትናንት በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ካናዳ እና ቦሲኒያ ሄርዞጎቪና አንድ አቻ ተለያይተዋል። ካናዳ ከኳታር፣ ስዊዘርላንድ ከቦሲኒያ ሄርዞጎቪና በቀጣይ በምድቡ የሚደረጉ ጨዋታዎች ናቸው።
የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን የሀገርን ስም የሚያስጠሩ ስፖርተኞችን የማፍራት ተግባሩን አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል - ሚኒስትር ሐና አርዓያሥላሴ
Jun 13, 2026 420
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን የሀገርን ሰንደቅ ዓላማ በዓለም አቀፍ መድረኮች ከፍ አድርገው የሚያውለበልቡ እውቅ አትሌቶችንና ስፖርተኞችን የማፍራት ተግባሩን አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የፍትሕ ሚኒስትር ሐና አርዓያሥላሴ ገለጹ። ሚኒስትሯ ይህን የተናገሩት የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን የስፖርት ክለብ እንዲሁም የሙዚቃና ቴአትር ቡድን የተመሠረቱበትን 40ኛ ዓመት በዓል ባከበሩበት መድረክ ላይ ነው። በመድረኩ ለታዋቂዋ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ የረዳት ኮሚሽነርነት ማዕረግ የተሰጠ ሲሆን፤ ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉን ጨምሮ በስፖርት ክለቡና በኪነ-ጥበብ ቡድኑ ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት ዕውቅና ተሰጥቷል። የፍትሕ ሚኒስትር ሐና አርዓያሥላሴ በዚህ ወቅት ባደረጉት ንግግር፤ የኮሚሽኑ የስፖርት ክለብ ባለፉት 40 ዓመታት በሀገሪቱ የስፖርት ታሪክ ውስጥ ደማቅ አሻራ ማሳረፉን ገልጸዋል። የሀገሪቱን ሰንደቅ ዓላማ በዓለም አቀፍ መድረኮች ከፍ ያደረጉ እውቅ አትሌቶችንና ስፖርተኞችን በማፍራት በኩል ተቋሙ የተጫወተው ሚና የላቀ መሆኑን ጠቅሰው፤ ኮሚሽኑ በስፖርትና በኪነ-ጥበብ ዘርፍ የጀመራቸውን አበረታች ሥራዎች ይበልጥ ዘመናዊ በማድረግ አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባው አስገንዝበዋል። የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽነር ጄኔራል የኑስ ሙሉ በበኩላቸው፤ ኮሚሽኑ በፍርድ ቤት ውሳኔ የሚላኩ ታራሚዎችን አምራችና ሕግ አክባሪ ዜጋ አድርጎ የማውጣት ትልቅ ሀገራዊ ኃላፊነት የተጣለበት ተቋም መሆኑን አስታውቀዋል። ይህን ኃላፊነት ለመወጣት በሚያደርገው ጥረት የስፖርት ክለቡ እንዲሁም የሙዚቃና ቴአትር ቡድኑ የሕግ ማረም ሥራውን በጥበብና በማስረጽ፣ እንዲሁም በስፖርት የአካል ብቃት በማጎልበት ታራሚውን እያዝናኑና እያስተማሩ በመቅረጽ በኩል ሚናቸው የላቀ ነው ብለዋል። ሁለቱም ክፍሎች በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ግንባር ቀደም ተዋናይ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በተለይም የስፖርት ክለቡ በሀገር ውስጥና በዓለም አቀፍ መድረኮች የሀገርን ስም ያስጠሩ በርካታ ጀግና ስፖርተኞችን ያፈራ መሆኑን ገልጸዋል። በአትሌቲክሱ ዘርፍ የመጀመሪያዋ አፍሪካዊትና ጥቁር ሴት የኦሎምፒክ ሻምፒዮን የሆነችውን ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉን፣ ረዳት ኮሚሽነር አትሌት ጥሩነሽ ዲባባን፣ አትሌት ስለሺ ስህን እንዲሁም የማራቶን ጀግናዋን ፋጡማ ሮባን ማፍራቱን በኩራት አስታውሰዋል። በተመሳሳይ መልኩ የሙዚቃና ቴአትር ቡድኑ በኢትዮጵያ ኪነ-ጥበብ ውስጥ ጎልቶ የሚታይ ደማቅ አሻራ ያሳረፉና ለሀገር ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረከቱ በርካታ የጥበብ ባለሙያዎችን ለሀገር ማበርከቱን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የፀረ-ዶፒንግ ትምህርት ጉባኤ ለማዘጋጀት ተመረጠች
Jun 13, 2026 398
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ በ2027 የሚካሄደውን ዓለም አቀፍ የፀረ-ዶፒንግ ትምህርትና ስልጠና ጉባኤ (Global Education Conference) እንድታስተናግድ መመረጧን የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ። ኢትዮጵያ ለስፖርት ልማት በተሰጠው ትኩረት ከፍተኛ ፋይዳ ያላቸውን ዓለም አቀፍ የስፖርት ኩነቶች ለማዘጋጀት ጥረት እያደረገች ትገኛለች። እ.ኤ.አ በ2027 የሚካሄደውን ዓለም አቀፍ የፀረ-ዶፒንግ ትምህርትና ስልጠና ጉባኤ (Global Education Conference) እንድታስተናግድ መመረጧን ሚኒስቴሩ አመልክቷል። በዓለም አቀፉ የፀረ-ዶፒንግ ኤጀንሲ (WADA) አዘጋጅነት በየጊዜው በመካሄድ ላይ የሚገኘው ይህ ዓለም አቀፍ ጉባኤ በፀረ-አበረታች ቅመሞች እንቅስቃሴ ውስጥ ከፍተኛ አንድምታ ያለው ሁነት መሆኑ ተገልጿል። ቀደም ሲል እ.ኤ.አ በ2018 በቻይና ቤጂንግ፣ በ2022 በአውስትራሊያ ሲድኒ እንዲሁም በ2024 በፈረንሳይ ሀገር መካሄዱ ይታወሳል። ይህ ጉባኤ በአፍሪካ ደረጃ ሲካሄድ የመጀመሪያው በመሆኑ ለኢትዮጵያ የገፅታ ግንባታ እና ለስፖርት ቱሪዝም እድገት ከሚያበረክተው አስተዋፅኦ በተጨማሪ፣ በአህጉር አቀፍ ደረጃ የፀረ-አበረታች ቅመሞች እንቅስቃሴውን የበለጠ በማጎልበትና ንፁህ ስፖርትን በማስፋፋት ረገድ ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወት ተነግሯል። ጉባኤው ኢትዮጵያ አበረታች ቅመሞችን ወይም ዶፒንግን የሚመለከቱ ጉዳዮችን በመደበኛ የትምህርት ስርዓት ውስጥ አካትቶ መተግበርን፣ በቂ የህግ ማዕቀፎችን በማውጣት ተግባራዊ ማድረግን፣ እንዲሁም ጠንካራ የምርመራና ቁጥጥር ስርዓት መዘርጋትና ተግባራዊ ማድረግን ጨምሮ ያስመዘገበቻቸውን በርካታ ውጤቶች ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በአግባቡ ለማስገንዘብ ተጨማሪ እድል እንደሚፈጥር የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል።
አዲስ አበባ የዓለም አቀፍ ውድድሮች ቀዳሚ ተመራጭ ከተማ
Jun 13, 2026 344
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ አዲስ አበባ አህጉራዊና ዓለም አቀፍ የስፖርት ውድድሮች በስፋት የሚስተናገዱባት ቀዳሚ ተመራጭ መሆን መቻሏን የከንቲባ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለስፖርቱ ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረትና ባከናወናቸው ግዙፍ የስፖርት መሠረተ ልማት ግንባታዎች ተመራጭ የስፖርት ማዕከል መሆን መቻሏን አመልክቷል። ባለፉት ዓመታት በከተማዋ የተገነቡት ከ1,580 በላይ የሕዝብና የወጣቶች ስፖርት ማዕከላት ማኅበረሰባዊ ተሳትፎን ከማሳደግ ባለፈ አገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ውድድሮችን ለማስተናገድ ትልቅ መሠረት መሆኑን ገልጿል። በቅርቡ በታላቅ ድምቀት የተጠናቀቀውና በመስቀል አደባባይ የተካሄደው 19ኛው የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶንን ጨምሮ ከተማዋ የተለያዩ ዓለም አቀፍ የብስክሌት፣ የአትሌቲክስ፣ የጎዳና ላይ ሩጫን ጨምሮ ሌሎች የስፖርት ሁነቶችን በስኬት በማስተናገድ መዲናዋ ምቹ ፥ እና ተመሪጭ ከተማ መሆኗን በተግባር እያሳየች ትገኛለች። አዲስ አበባ አሁን ላይ የስፖርት ልሂቃን መገናኛ ትላልቅ ውድድሮችንና ደጋፊዎችን የምታስተናግድ ደኅንነቷ የተጠበቀና ውብ መዲና ሆናለች ሲል ጽህፈት ቤቱ ገልጿል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በከተማ አስተዳደሩ የተከናወኑት የተቀናጁ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች፣ የወንዝ ዳርቻዎች እና ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ማዕከላት መስፋፋት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለስፖርት ቱሪዝም ዕድገት ትልቅ አቅም ፈጥረዋል። ይህ የስፖርት ቱሪዝም ዕድገት ከስፖርታዊ ፋይዳው ባሻገር፣ ለሆቴል ኢንዱስትሪው፣ ለትራንስፖርት ዘርፉና ለአካባቢው አነስተኛና ጥቃቅን የንግድ አንቀሳቃሾች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ መነቃቃትን መፍጠሩ ተመላክቷል። ይህም የከተማ አስተዳደሩ የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ የያዘውን ግብ በከፍተኛ ደረጃ እየደገፈው እንደሚገኝም ነው ጽሕፈት ቤቱ ያስታወቀው።