ቀጥታ፡
ስፖርት
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የ55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና አጠቃላይ አሸናፊ ሆነ
Mar 29, 2026 84
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ ከመጋቢት 15 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በአደይ አበባ ዓለም አቀፍ ስታዲየም ሲካሄድ የቆየው 55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ተጠናቋል። በሻምፒዮናው ላይ 36 ክለቦች፣ ተቋማት፣ 9 ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተሳተፉ ሲሆን፤ 621 ወንድ፣ 436 ሴት በድምሩ 1057 ተወዳዳሪዎች ተሳትፈዋል።   ሻምፒዮናው ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት፣ ለአትሌቶች የውድድር እድል ለመፍጠር ፣ አትሌቶችን በሽልማት የማበረታታት ዓላማ ያለው ነው። በውድድሩ ማብቂያ ቀን 10 የፍጻሜ ውድድሮች ተካሄደዋል።   ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሻምፒዮናው አጠቃላይ አሸናፊ በመሆን አጠናቋል። መቻል ሁለተኛ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሶስተኛ ደረጃን ይዘው መጨረሳቸውን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በሻምፒዮናው መዝጊያ ላይ የተገኙት የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ኮማንደር ስለሺ ስህን እና ሌሎች የፌዴሬሽኑ ከፍተኛ አመራሮች ለክለቦች እና አትሌቶች የተዘጋጁ የገንዘብ፣ የዋንጫና ሜዳሊያ ሽልማቶችን አበርክተዋል። ፌዴሬሽኑ ለውድድሩ ለማካሄድ 10 ሚሊዮን ብር ወጪ ማድረጉን አስታውቋል።   ዘመናዊ የሰዓት መመዝገቢያ ማሽን (Time Tronics) በሻምፒዮናው ላይ ተግባራዊ ሆኗል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ፌዴሬሽኑ በየዓመቱ ከሚያካሂዳቸው ውድድሮች መካከል በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው።
ዋልያዎቹ ከሞሮኮ መልስ የመጀመሪያ ልምምዳቸውን አድርገዋል
Mar 29, 2026 72
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቅድመ ማጣሪያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ለሚያደርገው የመልስ ጨዋታ የመጀመሪያ ልምምዱን ማምሻውን በድሬዳዋ ስታዲየም ሰርቷል።   በአባቱ ድንገተኛ ህልፈተ ሕይወት ምክንያት በመጀመሪያው ጨዋታ ያልነበረው የብሔራዊ ቡድኑ አምበል ጋቶቾ ፓኖም ስብስቡን ተቀላቅሎ ልምምድ አድርጓል። የዋልያዎቹ ተጋጣሚ የሆኑት ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ዛሬ ከቀትር በኋላ ድሬዳዋ መግባታቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።   የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች የመልስ ጨዋታ ማክሰኞ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ ከትናንት በስቲያ ሞሮኮ ላይ በተካሄደው የመጀመሪያ ጨዋታ 3 ለ 0 አሸንፋለች።   በአሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ የሚመራው ብሔራዊ ቡድን በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ ወደ ምድብ ድልድል መግባቱን ያረጋግጣል።   36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ በ2027 በታንዛንያ፣ ኬንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት ይካሄዳል።
በጅማ ዞን የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን የማስፋፋት ተግባር እየተከናወነ ነው
Mar 29, 2026 180
ጅማ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፡- በሥነ-ምግባርና በአካል የበቁ ወጣቶችን ለማፍራት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን የማስፋፋት ተግባር በትኩረት እያከናወነ መሆኑን የጅማ ዞን አስታውቋል።   32ኛው መላው የጅማ ዞን ስፖርት ሻምፒዮና በጅማ ከተማ መካሄድ የጀመረ ሲሆን፤ ሻምፒዮናው በእግር ኳስ፣ በማርሻል አርት እና በሌሎች 13 የስፖርት ዓይነቶች ለ15 ቀናት መካሄዱን ይቀጥላል።   የዞኑ ምክትል አሥተዳዳሪ ዩሱፍ ሻሮ በዚሁ ወቅት፤ ዞኑ የስፖርት ማዘውተሪያዎችን በመገንባትና ውድድሮችን በማዘጋጀት በሀገርና በክልል ደረጃ ተወዳዳሪ ብሎም ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት እየሠራ ነው ብለዋል። የጅማ ዞን ወጣቶችና ስፖርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ነጉማ መኮንን እንዳሉት፤ በስፖርት ሻምፒዮናው ከሁሉም የዞንና ወረዳዎች የተውጣጡ 1 ሺህ 800 ወጣቶች እየተሳተፉ ነው።   በውድድሩ ዞኑን ወክለው በክልል ደረጃ የሚሰለፉ ስፖርተኞች እንደሚመረጡም ጠቁመዋል።   ስፖርታዊ ሁነቶችን የምናካሂደው ሰላማችንን አስጠብቀን ስንቀጥል በመሆኑ፤ ለሰላም እና ለሀገር አንድነት ቅድሚያ ሰጥቶ መሥራት ይገባል ያሉት ደግሞ የኦሮሚያ ክልል የሥራና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ባይሳ ኩማ ናቸው።
ፌስቲቫሉ ኅብረ-ብሔራዊ አንድነት የሚጠናከርበትና አብሮነት የሚደምቅበት ነው
Mar 29, 2026 81
ሐረር፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፡- የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ኅብረ-ብሔራዊ አንድነት የሚጠናከርበት፣ የብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ዕሴትና አብሮነት የሚደምቅበት ነው ሲሉ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለጹ። 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድርና 19ኛው የባህል ስፖርት ፌስቲቫል "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሐሳብ በሐረር ከተማ ተጀምሯል፡፡   ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን በወቅቱ እንዳሉት፤ የኅብረ-ብሔራዊ አንድነትና አብሮነት መጠበቅና መረጋገጥ የባህል ስፖርቶችን አጉልቶ ለማሳየት ጠቃሚ ነው። የበለጠ እንዲጎለብትም መንግሥት ልዩ ትኩረት እንደሰጠው ተናግረዋል፡፡ የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴዔታ መክዩ መሀመድ በበኩላቸው፤ መንግሥት የባህል ስፖርትን ቀጣናዊ ትስስርን ለማምጣት፣ ወንድማማችነትንና እህትማማችነትን ለማጠናከር እየሠራበት ነው ብለዋል።   ኢትዮጵያ የ2026 የአፍሪካ የባህል ስፖርት ፌስቲቫልን የማስተናገድ ዕድል ማግኘቷንም አውስተዋል። ይህን ዕድል በመጠቀምም የባህል ስፖርቶቻችንን ለአፍሪካ እህት ወንድሞቻችን ለማስተዋወቅ ሥራዎች እየተሠሩ ነው ብለዋል። በሀገሪቱ ከ293 በላይ የተመዘገቡ ባህላዊ ስፖርቶችና ጨዋታዎች እንዳሉ በጥናት መለየቱን አረጋግጠዋል። ይሁን እንጅ የጨዋታ ሕግና ሥርዓት ተዘርግቶላቸው ለውድድር የበቁት ከ11 የስፖርት ዓይነቶች እንደማይበልጡ ጠቁመው፤ በቀጣይ ይህን ለማስፋት እንደሚሠራ አመላክተዋል። የባህል ስፖርት የሕዝብ ለሕዝብ ትስስርን በዘላቂነት በማጠናከር ረገድ ትልቁን ሚና እንደሚጫወት የገለፁት ደግሞ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርቶች ፌዴሬሽን ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሕይወት መሀመድ ናቸው፡፡ በሐረር ከተማ የተጀመረው የባህል ስፖርት ውድድርና ፌስቲቫል ለ8 ቀናት እንደሚቆይና ከመላ ሀገሪቱ የተውጣጡ ከ1 ሺህ 500 በላይ ስፖርተኞች ተሳትፎ እንደሚያደርጉበት ተናግረዋል።
ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል የመክፈቻ ስነ ስርዓት በሀረር ከተማ እየተካሄደ ነው 
Mar 29, 2026 86
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል የመክፈቻ ስነ ስርዓት በሀረር ከተማ ኢማም አህመድ ስታዲየም እየተካሄደ ይገኛል። ውድድር እና ፌስቲቫሉ የሚካሄደው "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ!" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው።   ስፖርታዊ ውድድሩ በሀረር ከተማ የተጀመረ ሲሆን በተለያዩ የጎዳና ላይ ትርዒቶችና የማርች ባንድ ሰልፍ ታጅቦ መካሄድ ጀምሯል። በውድድርና ፌስቲቫሉ መክፈቻ ላይ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ መኪዩ መሐመድ፣ የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ፣ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርቶች ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ወይዘሮ ህይወት መሐመድ እና የአፍሪካ ባህል ስፖርቶችና ጨዋታዎች ኮንፌዴሬሽን አመራሮች፣ የሁሉም ክልሎችና የሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች የወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊዎች፣ የክልሉ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ ከክልሉ የተለያዩ ወረዳዎች የተወጣጡ ነዋሪዎች ተገኝተዋል።   በ11 የስፖርት አይነት በሚካሄደው ውድድርና ፌስቲቫል ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ከ1500 በላይ ስፖርተኞች እንደሚሳተፉ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታውቋል። ፌስቲቫሉ ህብረተሰቡን በባህል ስፖርት ተሳታፊና ተጠቃሚ ከማድረግም ባሻገር የባህል ስፖርትን ማህበረሰብ አቀፍ የማድረግ አላማ ያለው ነው። ውድድሩና ፌስቲቫሉ እስከ መጋቢት 27 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ዛሬ ይጀመራል
Mar 29, 2026 155
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ከዛሬ ጀምሮ በሐረር ከተማ ይካሄዳል። የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን እና የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ስፖርታዊ ሁነቱን በጋራ አዘጋጅተዋል። ውድድሩና ፌስቲቫሉ "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ የሚደረግ ነው። በ11 የስፖርት አይነት በሚካሄደው ውድድርና ፌስቲቫል ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ከ1500 በላይ ስፖርተኞች እንደሚሳተፉ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታውቋል። በውድድርና ፌስቲቫሉ ላይ ከአፍሪካ ባህል ስፖርቶች እና ጨዋታዎች ኮንፌዴሬሽን የተጋበዙ የክብር እንግዶች ይታደማሉ። ሁነቱ የኢትዮጵያ ኅብረ ብሔራዊ አንድነት፣ ብዝሃነት እና አብሮነት የሚተዋወቅበት መሆኑ ተመላክቷል። ፌስቲቫሉ ህብረተሰቡን በባህል ስፖርት ተሳታፊና ተጠቃሚ ከማድረግም ባሻገር የባህል ስፖርትን ማህበረሰብ አቀፍ የማድረግ አላማ እንዳለው የሚኒስቴሩ መረጃ ያሳያል። መንግስት ለስፖርት ልማት በሰጠው ልዩ ትኩረት በአዲሱ የስፖርት ፖሊሲ አማካኝነት የባህል ስፖርቶችን ለማልማት እየሰራ እንደሚገኝም ተገልጿል።
ለቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ክለብ የ100 ሚሊየን ብር ድጋፍ ተደረገ
Mar 28, 2026 158
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ እና ቢጂአይ ኢትዮጵያ ለቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ክለብ የ100 ሚሊየን ብር ድጋፍ አደረጉ። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት የቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ክለብ ከገጠመው የመፍረስ አደጋ ለመታደግ የተለያዩ አካላትን በማስተባበር የ100 ሚሊየን ብር ድጋፍ መደረጉን አመልክተዋል።   ቅዱስ ጊዮርጊስ እግር ኳስ ክለብ የተጫዋቹ እና የማህበሩ ብቻ ሳይሆን አንዱ የከተማችን ጠንካራ ክለብ ነው ሲሉም ገልጸዋል። ኢትዮጵያንና ከተማዋን የወከለ ታሪካዊ የስፖርት ክለብ ከመፍረስ የመታደግ ኃላፊነት እንዳለብን እናምናለን ሲሉም ነው የተናገሩት ከንቲባዋ በመልዕክታቸው። ይህ አንጋፋ የስፖርት ክለብ ላለፋት 6 ወራት ደመወዝ መክፈል የማይችልበት ደረጃ ላይ ደርሶ እና የመበተን አደጋ ተጋርጦበት እንደነበር አውስተዋል።   በክለቡ ላይ የተጋረጠውን አደጋ ማየት ስለሌብን ከከተማው በጀትም ወስነን፣ ለባለሀብቶች ባቀረብነው ጥያቄ መሰረት ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ እና ቢጂአይ ኢትዮጵያ በሰጡን ፈጣን ምላሽ በጥቅሉ የ100 ሚሊየን ብር ድጋፍ ለተቋቋመው ጊዜያዊ ኮሚቴ አስረክበናል ነው ያሉት። ለከተማችን ወጣቶች፣ ለስፖርት ቢሮ እና ድጋፍ ላደረጉት ተቋማት በስፖርቱ ቤተሰብ ስም ምስጋናዬን ማቅረብ እወዳለሁ ሲሉም ገልጸዋል ከንቲባ አዳነች አቤቤ። ይህ ድጋፍ ከተማ አስተዳደሩ ክለቡን ከውድቀት ለመታደግና ለስፖርት ወዳድ ህዝብ የሰጠው ክብር አንዱ ማሳያ መሆኑንም ተናግረዋል።   ቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ክለብ ሁሉንም ባሳተፈ እና በግልፅነት አዲስ ቦርድ መርጦ ከገጠመው ጊዜያዊ ችግር ተላቆ ወደ ቀድሞ ጥንካሬውና ዝናው የሚመለስበት ጊዜ ቅርብ እንዲሆን እመኛለሁ ብለዋል ከንቲባዋ በመልዕክታቸው።
በክልሉ በስፖርት ዘርፍ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ -ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ
Mar 28, 2026 91
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በስፖርት ዘርፍ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በክልሉ ነገ የሚጀመረው 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል የዝግጅት ስራዎችን ተመልክተዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት በክልሉ በስፖርቱ ዘርፍ የሚከናወኑ ስራዎች በተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው፤ በዘርፉ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራትም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አንስተዋል።   በተለይ በክልሉና በአካባቢው በተለያዩ የስፖርት ዘርፍ ክህሎት ያላቸው ታዳጊ ስፖርተኞችን የማፍራት ስራ በትኩረት መስራት ይገባል ነው ያሉት። የሰርከስ ስፖርትን በማጎልበት በኩልም በሰፊው መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ከነገ ጀምሮ በሐረሪ ክልል ይካሄዳል። ለአንድ ሳምንት የሚቆየው የባህል ስፖርቶች ውድድር እና ፌስቲቫል "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ ይከናወናል።
ጣልያን ዴንማርክ እና ስዊድን ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ የጥሎ ማለፍ ፍጻሜ አለፉ 
Mar 27, 2026 106
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ዞን የመጀመሪያ ዙር የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። በቤርጋሞ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጣልያን ሰሜን አየርላንድን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ሳንድሮ ቶናሊ እና ሞይስ ኪን ጎሎቹን አስቆጥረዋል። በሌላኛው መርሐ ግብር ዴንማርክ ሰሜን ሜቄዶናያን 4 ለ 0 ረታለች።   በፓርከን ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ጉስታቭ ኢሳክሰን ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሚኬል ዳምስጋርድ እና ክርስቲያን ኖርጋርድ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ስዊድን ዩክሬንን 3 ለ 1 አሸንፋለች።   በቫሌንሺያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአርሰናሉ አጥቂ ቪክቶር ዮኮሬሽ ሁለት ግቦችን በጨዋታ ቀሪውን ጎል በጨዋታ በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ማትቪይ ፖኖማሬንኮ ለዩክሬን ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ፖላንድ በሮበርት ሎዋንዶውስኪ እና ፒተር ዚሊኒሲኪ ጎሎች አልባኒያን 2 ለ 1 አሸንፋለች።   አርበር ሆክስሃ ለአልባኒያ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በሌሎች ጨዋታዎች ኮሶቮ ስሎቫኪያን 4 ለ 3 ስትረታ ቼክ ሪፐብሊክ አየርላንድን፣ ቦሲኒያ እና ሄርዞጎቪና ዌልስን በተመሳሳይ በመለያ ምት አሸንፈዋል። ውጤቶቹን ተከትሎ ጣልያን፣ ዴንማርክ፣ ስዊድን፣ ፖላንድ ፣ ቼክ ሪፐብሊክ፣ ቦሲኒያ እና ሄርዞጎቪና እንዲሁም ኮሶቮ ለፍጻሜ ጨዋታ አልፈዋል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ ቱርኪዬ ሮማንያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ጣልያን ከቦሲኒያ እና ሄርዞጎቪና፣ ፖላንድ ከስዊድን፣ ቱርኪዬ ከኮሶቮ እና ዴንማርክ ከቼክ ሪፐብሊክ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ለዓለም ዋንጫው ለማለፍ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በጥሎ ማለፉ የሚያሸንፉ አራት ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ።
"ቪዚት ሐረር" የጎዳና ላይ የሩጫ ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ተካሄደ
Mar 27, 2026 90
ሐረር፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፡- የሹዋሊድ በዓልን ምክንያት በማድረግ "ቪዚት ሐረር" የተሰኘ የጎዳና ላይ የሩጫ ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ተካሂዷል። የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ፌስቲቫሉ፤ በርካታ የክልሉ ነዋሪዎች፣ አመራር አካላት፣ አትሌቶች፣ ታዳጊ ሕጻናት፣ ወጣቶችንና ሌሎችን አሳትፏል። የጎዳና ላይ የሩጫ ፌስቲቫሉን ያስጀመሩት የክልሉ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ተውፊቅ መሀመድ እንዳሉት፤ የሩጫ ፌስቲቫሉ አብሮነትን የሚያጠናክር ነው። የሐረሪ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙራድ አብዲ በበኩላቸው፤ የሹዋሊድ በዓልን በማስመልከት የተዘጋጀው የሩጫ ፌስቲቫል በሐረር የሚገኙ የመስኅብ ስፍራዎችን ለማስተዋወቅና እንዲጎበኙ ለማድረግ ታስቦ መዘጋጀቱን አስረድተዋል። ይህም በክልሉ የሚገኙ ጥንታዊ፣ ባህላዊና ታሪካዊ የመስኅብ ስፍራዎችን ይበልጥ ለማስተዋወቅ ይረዳል ብለዋል። በፌስቲቫሉ አሸናፊ ለሆኑ ተወዳዳሪዎች የሜዳሊያና የዋንጫ ሽልማት ተበርክቷል።
የስፖርት እንቅስቃሴ ባህልን የቀየሩት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች    
Mar 27, 2026 98
በመዲናዋ የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ስራዎች የከተማውን ገጽታ በመቀየር ውብ እንድትሆን እያደረጓት ይገኛሉ። በዚህም በርካታ መዝናኛ ስፍራዎችና ስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ ነው። እነዚህ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ቀንም ሆነ ማታ አገልግሎት መስጠት የሚያስችሏቸው መሰረተ ልማቶች ተሟልተውላቸው አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ። በስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ሲያደርጉ ያገኘናቸው ወጣቶች ለኢዜአ እንዳሉት፤ ማዘውተሪያዎቹ በጀመሩት የምሽት አገልግሎት ከስራ መልስ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ጤናችን እንድንጠብቅ አስችሎናል። በከተማው የምሽት አገልግሎት መስጠት ከጀመሩት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች መካከል በየካ ክፍለ ከተማ የሚገኝ 28 ሜዳ አንዱ ነው። በሜዳው ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ከሚያደርጉ ወጣቶች መካከል ያሬድ ስጦታው ከጓደኞቹ ጋር በመሆን ለበርካታ ዓመታት ስፖርታዊ እንቅስቃሴ የሚያደርጉበት ሜዳ መሆኑን ገልጿል። ሜዳው ከዚህ ቀደም ጥራቱን ያልጠበቀና ምንም ዓይነት እድሳት ያልተደረገለት እንደነበርም ያስታውሳል። አሁን ግን ሜዳው ጥራቱን የጠበቀና ምሽትን ጨምሮ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሰረተ ልማት ተሟልቶለት እስከ ምሽት እስከ 4 ሰዓት እንድንጫወት አስችሎናል ይላል። ወጣት ዳዊት ደማሙና አቤል ነጋሲ በበኩላቸው፤ የስፖርት ማዘውተሪያው የምሽት አገልግሎት መስጠት መጀመር ቀን ስራ ውለን ማታ ጊዜያችንን በስፖርት እንቅስቃሴ እንድናሳልፍ አድርጎናል ብለዋል። ይህም ከአብሮ አደግ ጓደኞቻችን ጋር ያለን ኅብረት እንድናጎለብት አስችሎናል ይላሉ። በየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ ሰባት የሚገኘው የስፖርት ማዘውተሪያም በምሽት አገልግሎት እየሰጠ ነው። በዚሁ ወቅት ወጣት ተከተል ታዬ እንዳለው፤ ሜዳው ከዚህ ቀደም በአካባቢው ያልነበረና የኮሪደር ልማቱን ተከትሎ የተገነባ ነው። በተለይም በምሽት አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሰረተ ልማቶች መያዙ ማታ ከስራ መልስ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ጤናችን እንድንጠበቅ እያስቻለን ነው ብሏል። በዚህም ከእኩዮቹ ጋር ስፖርታዊ እንቅስቃሴ የሚያደርጉበት የጤና ቡድን መስርተው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጿል። የስፖርት ማዘውተሪያው አገልግሎት ከረዥም ጊዜ በኋላ ወደ ስፖርት እንድመለስ አድርጎኛል በማለት የገለጸው ደግሞ ወጣት ማይክ ብርሃኔ ነው። የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ፤ በመዲናዋ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች የስፖርት ማዘውተሪያ እጥረት ከመቅረፍ ባሻገር ለከተማዋ ተጨማሪ ድምቀት መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የከተማዋ ወጣቶችም አልባሌ ቦታ እንዳይውሉና ጤናቸውን እንዲጠብቁ በማድረግ በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ የስፖርት ማዘውተሪያዎቹ የምሽት አገልግሎት መስጠት መጀመራቸው በተለይም ነዋሪዎች ከስራ መልስ ምቹ በሆነ ሜዳ ላይ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ የሚያደርጉበት ቦታ መኖሩ በርካታ ጥቅሞችን እያስገኘ ነው ብለዋል።   በቀጣይም የስፖርት ማዘውተሪያና መዝናኛዎችን የማስፋፋት እንዲሁም የወጣት ስብዕና መገንቢያ ማዕከላትን የማዘመን ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
ጃማይካ እና ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ የፍጻሜ ጨዋታ አለፉ
Mar 27, 2026 86
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም የክፍለ አህጉራት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሜክሲኮ ተካሄደዋል። ዛሬ ማለዳ በአክሮን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጃማይካ ኒው ካሌዶኒያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ባይሊ ካዳማርቴሪ በ18ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ጃማይካ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እጅሎችን በመፍጠር ከተጋጣሚዋ ኒው ካሌዶኒያ ተሽላ ተገኝታለች። ትናንት ከእኩለ ሌሊት በኋላ በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ቦሊቪያ ሱሪናምን 2 1 ረታለች።   በቢቢቪኤ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሞሰስ ፓኒያጉአ በጨዋታ እና ሚጉዌል ቴርሴሮስ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሊያም ቫን ጌልደርን ለሱሪናም ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቶቹን ተከትሎ ጃማይካ እና ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ፍጻሜ አልፈዋል። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከጃማይካ እና ኢራቅ ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ መጋቢት 18 ቀን 2018 ዓ.ም በሜክሲኮ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ ያላቸው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ኢራቅ አስቀድመው ለፍጻሜው ጨዋታ ማለፋቸው ይታወቃል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ትጫወታለች
Mar 27, 2026 135
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የመጀመሪያ ጨዋታዋን ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ዛሬ ታደርጋለች። የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታ በሞሮኮ ኤል አብዲ ስታዲየም ምሽት 1 ሰዓት ላይ ይካሄዳል። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ ጁን 2027 በኬንያ ፣ ዩጋንዳና ታንዛንያ ጣምራ አዘጋጅነት ይከናወናል። በአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ 12 አገራት የደርሶ መልስ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ከጨዋታዎቹ መካከል ኢትዮጵያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር የምታደርገው ይገኝበታል። የሁለቱ ሀገራት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛሬ ይካሄዳል። ብሄራዊ ቡድኖቹ በውድድር ጨዋታዎች ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ባደረጓቸው ሁለት ጨዋታዎች በተመሳሳይ አንድ ጊዜ አሸንፈዋል። ሩሲያ እ.አ.አ በ2018 ባዘጋጀቸው 21ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የአፍሪካ ዞን ማጣሪያ ላይ ተገናኝተው ኢትዮጵያ በድምር ውጤት 3 ለ 1 በማሸነፍ ቀጣዩን ዙር መቀላቀሏ የሚታወስ ነው። በመጀመሪያው ጨዋታ ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ 1 ለ 0 ስታሸንፍ ኢትዮጵያ በመልሱ ጨዋታ 3 ለ 0 አሸንፋለች።   ዮሐንስ ሳህሌ በታህሳስ ወር 2018 ዓ.ም በሁለት ዓመታት የውል ጊዜ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው በይፋ መሾማቸው ይታወቃል። አዲሱ አሰልጣኝ የመጀመሪያ ጨዋታቸውን ዛሬ ያደርጋሉ። አሰልጣኝ ዮሐንስ ለጨዋታዎቹ ጥሪ ያደረጉላቸው ተጫዋቾች ለስምንት ቀናት በአዲስ አበባ ልምምዳቸውን አድርገዋል። ብሄራዊ ቡድኑ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት ማምሻውን በኤል አብዲ ስታዲየም ማድረጉን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በ47 ዓመቱ ፓርቹጋላዊ ሪካርዶ ሞናሳንቶ የሚመራው የሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ብሄራዊ ቡድን ለጨዋታ ለአንድ ሳምንት ያህል ልምምዱን አከናውኗል። በፊፋ ወርሃዊ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ ሳኦ ቶሜ እና ፕሪንሲፔ 189ኛ ደረጃን ይዛለች። ኢትዮጵያ 147ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። ሁለቱ ብሄራዊ ቡድኖች የመልስ ጨዋታቸውን መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ያደርጋሉ። በደርሶ መልስ የሚያሸንፈው ሀገር ወደ ምድብ ድልድል ምዕራፍ ማለፉን ያረጋግጣል።
23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ይካሄዳል
Mar 26, 2026 157
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ከመጋቢት 20 እስከ 27 ቀን 2018 ዓ.ም በሐረር ከተማ እንደሚካሄድ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ። የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ መኪዩ መሐመድ ውድድሩንና ፌስቲቫሉን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል። ሚኒስትር ዴኤታው መንግስት ለስፖርት ልማት በሰጠው ልዩ ትኩረት በአዲሱ የስፖርት ፖሊሲ አማካኝነት የባህል ስፖርቶችን ለማልማት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ሁነቱ የኢትዮጵያን ህብረ ብሄራዊ አንድነት፣ ብዝሃነት እና አብሮነት የሚተዋወቅበት መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ህይወት መሐመድ በበኩላቸው ውድድሩና ፌስቲቫሉ ህብረተሰቡን በባህል ስፖርት ተሳታፊና ተጠቃሚ ከማድረግም ባሻገር የባህል ስፖርትን ማህበረሰብ አቀፍ የማድረግ አላማ እንዳለው ገልጸዋል። በውድድርና ፌስቲቫሉ ከአፍሪካ ባህል ስፖርቶች እና ጨዋታዎች ኮንፌዴሬሽን የተጋበዙ የክብር እንግዶች እንደሚታደሙበት ጠቁመዋል። በ11 የስፖርት አይነት በሚካሄደው ውድድርና ፌስቲቫል ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ከ1500 በላይ ስፖርተኞች ይሳተፋሉ። ሁነቱ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ነው። ውድድሩና ፌስቲቫሉ "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ እንደሚካሄድ የሚኒስቴሩ መረጃ ያመለክታል።
ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 26, 2026 76
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ድሬዳዋ ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአርባምንጭ ከተማዋ መድሃኒት ዓለሙ በ79ኛው ደቂቃ በራሷ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። የድሬዳዋ ከተማዋ መዓዛ አብደላ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጣለች። ከአምስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ድሬዳዋ ከተማ በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 10ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ ባለፉት 14 የሊጉ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ይርጋጨፌ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 4 ለ 2፣ ቦሌ ክፍለ ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 21ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከመጋቢት 28 እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም በቱርክዬ በሚከናወነው የዩኤፋ የወዳጅነት ዋንጫ ዝግጅት እና ተሳትፎ ያደርጋል። በብሔራዊ ቡድኑ ተሳትፎ ምክንያት የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ እንደሚቋረጥ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም