ቀጥታ፡
ስፖርት
ባህር ዳር ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድል ቀንቷቸዋል
May 15, 2026 64
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተካሄደዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ባህር ዳር ከተማ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ፍፁም ፍትዓለው እና አንተነህ ተፈራ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን ያስመዘገበው ባህር ዳር ከተማ በ44 ነጥብ ደረጃውን ከ9ኛ ወደ 6ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ34 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም የተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሸገር ከተማን 2 ለ 1 ረቷል። አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል ለንግድ ባንክ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቢንያም ፍቅሩ የሸገር ከተማን የማስተዛዘኝ ግብ አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ድሉን ያገኘው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ41 ነጥብ ከነበረበት 14ኛ ደረጃ ወደ 11ኛ ከፍ ብሏል። በሊጉ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሸገር ከተማ ደግሞ በ40 ነጥብ ከ12ኛ ደረጃ ወደ 13ኛ ወርዷል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጫዋቾቹ አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል በሊጉ ያስቆጠሩትን የግብ መጠን በተመሳሳይ 11 በማድረስ፣ በ14 ግቦች የከፍተኛ ግብ አግቢነቱን ደረጃ እየመራ የሚገኘውን የሲዳማ ቡናውን አቤል ያለውን ይከተላሉ። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ የ32ኛ ሳምንት ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ ተለያይተዋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች
May 15, 2026 150
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። የዕለቱ ቀዳሚ መርሐ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድንን ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ያገናኛል። መቀሌ 70 እንደርታ በ30 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ኢትዮጵያ መድን በ40 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች አሸንፏል። ጨዋታው መቀሌ 70 እንደርታ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ኢትዮጵያ መድን በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው። ድሬዳዋ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ያላገኘው ድሬዳዋ ከተማ በ34 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሉ። ባህር ዳር ከተማ በ41 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ባህር ዳር ከተማ በዘንድሮው የውድድር ዓመት በርካታ የአቻ ውጤቶችን (17 ጊዜ) ያስመዘገበ ቡድን ነው። ሁለቱም ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ38 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሸገር ከተማ በ40 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኢትዮጵያ መድን የ2 ለ 1 ሽንፈት ሲያስተናግድ ሸገር ከተማ የሊጉን መሪ ሲዳማ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታው ንግድ ባንክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ሸገር ከተማ በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የማጠናቀቂያ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ
May 15, 2026 115
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይደረጋሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ልደታ ክፍለ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ይጫወታሉ። ልደታ ክፍለ ከተማ በ22 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በ19 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በ26ኛ ሳምንት ወራጁን አርባምንጭ ከተማን 4 ለ 1 ያሸነፈው ልደታ ክፍለ ከተማ ዓመቱን በድል ለመቋጨት ይጫወታል። በ26ኛ ሳምንት በአዲስ አበባ ከተማ 3 ለ 1 የተሸነፈው ባህር ዳር ከተማ ዓመቱን ድል ለማሳረግ ወደ ሜዳ ይገባል። በሌላኛው መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና በ35 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ መውረዱ የተረጋገጠው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። በ25ኛ ሳምንት ይርጋጨፌ ቡና ያለ ግብ አቻ የተለያየው ሲዳማ ቡና ዓመቱን በማሸነፍ ለመፈጸም ይጫወታል። ከፕሪሚየር ሊጉ ለወረደው አርባምንጭ ከተማ ጨዋታው ከመርሐ ግብር ማሟያነት የዘለለ ትርጉም የለውም። ሃዋሳ ከተማ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሃዋሳ ከተማ በ49 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ43 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች ዓመቱን በድል ለማጠናቀቅ የሚያደርጉት ፍልሚያ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ66 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በተመሳሳይ 66 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰሎሞን በ24 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራች ይገኛል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ ደግሞ በ20 ግቦች ተከታዩን ስፍራ ይዛለች።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዝግጅት
May 14, 2026 227
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከብሩንዲ ጋር ለሚያደርገው ሁለተኛ ዙር የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታ የሁለተኛ ቀን ልምምዱን ዛሬ አድርጓል። አሰልጣኝ ራውዳ ዓሊ ለ30 ተጫዋቾች ጥሪ በማድረግ ትናንት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሜዳ ዝግጅታቸውን የጀመሩ ሲሆን ጥሪ የተደረገላቸው ተጫዋቾች ሁሉም ተገኝተው ልምምዳቸውን አከናውነዋል። በብሔራዊ ቡድኑ የሁለተኛ ቀን ዝግጅት ተጫዋቾች የእርስ በእርስ ጨዋታዎችን በማድረግ አቋማቸውን መፈተሻቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከብሩንዲ ጋር ግንቦት 16 የመጀመሪያ ጨዋታውን በሜዳው፣ የመልስ ጨዋታውን ግንቦት 23 ቡጁምቡራ ላይ ያከናውናል። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። በማጣሪያ የሚያልፉ አራት የአፍሪካ ሀገራት በሶስት ዙሮች በሚደረጉ ጨዋታዎች ይለያሉ።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሶስተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 14, 2026 164
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ ሶስተኛ ቀኑን ባስቆጠረው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተለያዩ ውድድሮች በመካሄድ ላይ ናቸው። ማምሻውን በተደረገው የ3000 ሜትር መሰናክል የወንዶች የፍጻሜ ውድድር አትሌት ገመቹ ጎዳና 8 ደቂቃ ከ41 ሴኮንድ ከ02 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ ወጥቷል። አትሌት ገመቹ ለኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ሶስተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አስገኝቷል። በውድድሩ ላይ የተሳተፈው ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ሳሙኤል ፍሬው ሶስተኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳሊያ ባለቤት ሆኗል። በ800 ሜትር ሴቶች ፍፃሜ አትሌት ምስጋና ኃይሉ እና በ400 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ አትሌት አጃይባ አልዩ የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘታቸው ይታወቃል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው ሶስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና ሶስት የነሐስ በድምሩ ሰባት ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
አንጋፋው የእግር ኳስ ሰው ጌታቸው ገብረማርያም ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ
May 14, 2026 159
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ የቀድሞ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጫዋች፣ ዓለም አቀፍ ዳኛ እና አመራር የነበሩት ጌታቸው ገብረማርያም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ጌታቸው ገብረማርያም በተጫዋችነት ለኦሜድላ እና ጥጥ ማኅበር እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተጫውተው ያሳለፉ ሲሆን በመቀጠል ለረጅም ዘመናት በዓለም አቀፍ ዳኝነት ጭምር በሚታወቁበት የዳኝነት ሙያ አገልግለዋል። ከዳኝነት ከተገለሉ በኋላም በኮሚሽነርነት፣ በአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንትነት እንዲሁም በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የተለያዩ የሥራ ኃላፊነቶች በጥቅሉ ከ60 ዓመታት በላይ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ላይ በማገልገል ማሳለፋቸውን ፌዴሬሽኑ ገልጿል። የአቶ ጌታቸው ገብረማርያም ሥርዓተ ቀብር ነገ በአማኑኤል ቤተ-ክርስቲያን ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ይፈፀማል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በአንጋፋው የእግር ኳስ ሰው ጌታቸው ገብረማርያም ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን በመግለጽ ለቤተሰብ፣ ለወዳጅ ዘመድ፣ ለእግር ኳስ ቤተሰብ እና ለሙያ ባልደረቦች መፅናናትን ተመኝቷል።
መቻል ወደ ሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና የተጠጋበትን ወሳኝ ድል አስመዘገበ
May 14, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር መቻል ነገሌ አርሲን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቸርነት ጉግሳ፣ በረከት ደስታ፣ ዩጋንዳዊው ቻርልስ ሙሲጌ እና ፈቱዲን ጀማል (በፍጹም ቅጣት ምት) ግቦቹን አስቆጥረዋል። ከተከታታይ የአቻ ውጤቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው መቻል በ52 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። መቻል ከመሪው ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት በማጥበብ የዋንጫ ተፎካካሪነቱን አጠናክሯል። በውድድር ዓመቱም 13ኛ ድሉን አስመዝግቧል። ከተከታታይ ድሎች በኋላ ሽንፈት ያስተናገደው ነገሌ አርሲ በ51 ነጥብ ከሁለተኛ ደረጃ ወደ ሶስተኛ ዝቅ ብሏል። በሊጉም ሰባተኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በዋንጫ ፉክክሩም ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥሏል። ዛሬ በተደረጉ የ32ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ሀዲያ ሆሳዕና የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡናን፣ ምድረ ገነት ሽሬ ኢትዮጵያ ቡናን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ወላይታ ድቻ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም