ቀጥታ፡
ስፖርት
አርጀንቲናው ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ ከብሔራዊ ቡድኑ ራሱን አገለለ
Aug 31, 2026 78
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የ39 ዓመቱ ሊዮኔል ሜሲ ከአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ራሱን ማግለሉን ይፋ አድርጓል። ሜሲ በኢንስታግራም ገጹ ባሰፈረው መልዕክት ከፍጻሜው ጨዋታ አንስቶ ነገሮችን በጥልቀት ካሰብኩ በኋላ፣ ከብሔራዊ ቡድን ራሴን ማግለሌን ለሁሉም ማሳወቅ እፈልጋለሁ ሲል ተናግሯል። ውሳኔው ውስጤን ቢጎዳውም እና በጣም ስሜታዊ የሚያደርገኝ ቢሆንም ራሴን የማግለሉ ጊዜ አሁን ነው ብሏል። የአርጀንቲናን ማልያ ለብሼ የምችለውን ሁሉ አድርጊያሁ፣ አርጀንቲናዊ በመሆናችሁ ኩራት እንዲሰማችሁ ለማድረግም ሁሉንም ነገር ሰጥቻለሁ ብሏል። ሜሲ አያይዞም የብሔራዊ ቡድን ቆይታው ሁልጊዜ በልቡ እንደሚኖር ገልጾ፣ አሁን ላይ አዲስ እና ወጣት ተጫዋቾች ዕድሉን ማግኘት እንዳለባቸው አንስቷል። ይህንን የስንብት ጽሑፍ የጻፈው ከዓለም ዋንጫው ፍጻሜ ጨዋታ ከሁለት ቀናት በኋላ እንደነበር ገልጾ፣ ከአባቱ ሞት በኋላ እያሳለፈው ያለው ጊዜ ዛሬ ላይ ውሳኔውን እንዲያሳልፍ እንዳስገደደው አመልክቷል። በእነዚህ 20 ዓመታት ውስጥ አርጀንቲናውያን ላሳዩት ፍቅር ምስጋና ያቀረበ ሲሆን ከብሔራዊ ቡድኑ ጎን በመልካምም በክፉም ጊዜ እንደሚቆም ተናግሯል። የሜሲ ውሳኔ የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን መነጋገሪያ ሆኗል። ሊዮኔል ሜሲ ከእ.አ.አ ከ2005 እስከ 2026 በአርጀንቲና ማልያ ባደረጋቸው 207 ጨዋታዎችን 125 ጎሎችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የምንጊዜም የሀገሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኗል። በአርጀንቲና ማልያ 65 ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ አቀብሏል። በቅርቡ በተካሄደው 23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ስምንት ጎሎችን ያስቆጠረ ሲሆን በአጠቃላይ በውድድሩ ላይ 22 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ከፈረንሳዊው ኪሊያን ምባፔ (23 ጎሎች) በመቀጠል በዓለም ዋንጫው የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ደረጃ ዝርዝር ውስጥ ተቀምጧል። ሊዮኔል ሜሲ በታሪኩ በአጠቃላይ 46 ዋንጫዎችን በማንሳት በእግር ኳስ ታሪክ ከፍተኛውን የዋንጫ ብዛት የሰበሰበ ባለክረብ-ወሰን ተጫዋች ነው። ሊዮኔል ሜሲ ከአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ጋር በአጠቃላይ የተለያዩ ዋንጫዎችን አንስቷል። የፊፋ ዓለም ዋንጫ ፣ ሁለት የኮፓ አሜሪካ ዋንጫዎች፣ የአውሮፓ እና ደቡብ አሜሪካ ሻምፒዮናዎችን ያገናኘው የፋይናሊሲማ ዋንጫ፣ እንዲሁም የኦሊምፒክ የወርቅ ሜዳሊያ እና ከ20 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ክብርን ተጎናጽፏል። ሊዮኔል ሜሲ በአሁኑ ሰዓት ለአሜሪካው ኢንተር ሚያሚ ክለብ እየተጫወተ ይገኛል።
አስቶንቪላ ከአርሰናል ፡- የሳምንቱ ተጠባቂ የሊግ ፍልሚያ
Aug 31, 2026 133
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ዛሬ ምሽት አራት ሰዓት ላይ አስቶንቪላ ከአርሰናል በቪላ ፓርክ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። አስቶንቪላ በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታው በብራይተን የ4 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ሻምፒዮኑ አርሰናል የዋንጫ ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን ኮቨንተሪ ሲቲን 3 ለ 0 በመርታት ጀምሯል። አስቶንቪላ በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት ቁልፍ ተጫዋቾቹን ማጣቱ ስብስቡ ላይ መሳሳት ፈጥሯል። ሞርጋን ሮጀርስ፣ ኦሊ ዋትኪንዝ፣ ኤሚሊያኖ ማርቲኔዝ፣ ኤዝሪ ኮንሳ፣ ዩሪ ቲሊማንስ፣ ሉካስ ዲኝ እና ዶኒየል ማለን አስቶንቪላን የለቀቁ ተጫዋቾች ናቸው። ኒኮላስ ጃክሰን፣ ሊኦን ጎሬትዝካ፣ አሮን ዋን-ቢሳካ፣ ማቴዎ ሩጌሪ አሌሃንድሮ ጋርናቾ (ውሰት ማንችስተር ዩናይትድ) ጨምሮ የተለያዩ ተጫዋቾችን በማስፈረም አቅሙን ለማጠናከር እየሰራ ነው። አርሰናል በበኩሉ ብሩኖ ጉማሬሽ፣ ክሪስቶስ ዞሊስ፣ ኤዝሪ ኮንሳ፣ ፒዬሮ ሂንካፒዬ እና ኢላን ሜስሊየርን በማስፈረም ስብስቡን አጠናክሯል። ክሪስቶስ ዞሊስ በመጀመሪያው የሊጉ ጨዋታ መልካም እንቅስቃሴ አድርጓል። ሁለቱ ክለቦች ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 54 የሊግ ጨዋታዎች መካከል አርሰናል 29ኙን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። አስቶንቪላ 11 ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ 14 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። አርሰናል በ54ቱ ጨዋታዎች ላይ 92 ግቦችን ሲያስቆጥር አስቶንቪላ በበኩሉ 48 ጎሎችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ባለፉት አምስት የሊግ ግንኙነታቸው አርሰናል በሶስቱ ሲያሸንፍ አስቶንቪላ አንድ ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። ክለቦቹ ባለፈው የውድድር ዓመት ባደረጓቸው ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አርሰናል ሁለቱንም አሸንፏል። ከዝውውር እንስቃሴዎችና ከወቅታዊ ብቃት አንጻር አርሰናል የማሸነፍ የቅድሚያ ግምቱን አግኝቷል። ተጋጣሚው አስቶንቪላ ከመጀመሪያ የሊግ ሽንፈቱ በኋላ በሜዳው የሚያደርገው ጨዋታ ጠንካራ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችለው መልካም አጋጣሚ ነው። የ39 ዓመቱ አውስትራሊያዊ ጃሬድ ጊሌት ተጠባቂውን ጨዋታ በመሐል ዳኝነት እንዲመሩ ተመድበዋል።
ማንችስተር ዩናይትድ በብሩኖ ፈርናንዴዝ ሀትሪክ ታግዞ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን አስመዘገበ
Aug 30, 2026 235
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ ኤፕስዊች ታውንን 5 ለ 2 ረትቷል። ማምሻውን በኦልትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብሩኖ ፈርናንዴዝ ሶስት ግቦችን (አንድ በፍጹም ቅጣት ምት) በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። የ31 ዓመቱ አማካይ በአዲሱ የውድድር ዓመት ሀትሪክ የሰራ የመጀመሪያ ተጫዋች ሆኗል። ብሪያን ምቡሞ እና የኤፕስዊቹ ጃኮብ ግሪቭስ በራሱ ላይ ቀሪዎቹን ጎሎች ለማንችስተር ዩናይትድ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሀትሪክ የሰራው ፈርናንዴዝ ለሙቤሞ ጎል ኳስ አመቻችቶ አቀብሏል።የጨዋታው ኮከብ በመባልም ተመርጧል። ሌፍ ዴቪስ እና ቹባ አክፖም የኤፕስዊችን ጎሎች ከመረብ ጋር አገናኝተዋል። በመጀመሪያው አጋማሽ ብልጫ ተወስዶበት የነበረው ማንችስተር ዩናይትድ በሁለተኛው አጋማሽ ፍጹም የበላይነት ወስዶ ተጫውቷል። ውጤቱን ተከትሎ ዩናይትድ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን አግኝቷል። አዲስ አዳጊው ኤፕስዊች ታውን በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ማንችስተር ዩናይትድ ከኤቨርተን፣ ኤፕስዊች ታውን ከሊቨርፑል ጋር ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ቼልሲ ተከታታይ ድሉን አስመዘገበ
Aug 30, 2026 135
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ቼልሲ ብራይተንን 4 ለ 3 ረትቷል። በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሮሚዮ ላቪያ፣ ፔድሮ ኔቶ፣ ጆአኦ ፔድሮ እና ኮል ፓልመር ለሰማያዊዎቹ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ማሊክ ያልኩዬ፣ ፓስካል ግሮስ እና የቼልሲው ጆአኦ ፔድሮ በራሱ ላይ የብራይተንን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ባለሜዳው ቼልሲ የበላይነት ወስዶ ተጫውቷል። ጨዋታው በርካታ የግብ እድሎች የተፈጠሩበት ነበር። ብራይተን በሁለተኛው አጋማሽ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ያደረገው ጥረት አልተሳካም። ተቀይሮ የገባው የቼልሲው ሞሰስ ካይሴዶ ጉዳት አጋጥሞት ተቀይሮ ወጥቷል። የምዕራብ ለንደኑ ቼልሲ በሊጉ ተከታታይ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ ብራይተን የውድድር ዓመቱን የመጀመሪያ ሽንፈት አስተናግዷል። በስታዲየም ኦፍ ላይት በተደረገው ጨዋታ ሰንደርላንድ ፉልሃምን 1 ለ 0 አሸንፏል። ዊልሰን ኢሲዶር በ75ኛው ደቂቃ ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሰንደላንድ በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ሶስት ነጥቡን ወደ ካዝናው አስገብቷል። የለንደኑ ፉልሃም ተከታታይ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በሌላኛው መርሐ ግብር ሊድስ ዩናይትድ እና ብሬንትፎርድ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በኢላንድ ሮድ በተካሄደው ጨዋታ ዶምኒክ ካልቨርት-ሉዊን ለሊድስ እና ኬቨን ሻደ ለብሬንትፎርድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታቸው ያሸነፉት ሁለቱ ክለቦች አንድ ነጥብ አሳክተዋል። ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ማንችስተር ዩናይትድ ከኤፕስዊች ታውን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
አዲሱ ጎበና የሲድኒ ማራቶን የስፍራውን ክብረወሰን በማሻሻል አሸነፈ
Aug 30, 2026 126
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፦በዓለም አትሌቲክስ የሜጀር ደረጃ በተሰጠው የሲድኒ ማራቶን በኢትዮጵያዊው አትሌት አዲሱ ጎበና አሸናፊነት ተጠናቋል። ለ24ኛ ጊዜ በተካሄደው በዚህ ውድድር አዲሱ ጎበና ርቀቱን 2 ሰዓት 04 ደቂቃ ከ42 ሴኮንድ በሆነ ፈጣን ሰዓት በማጠናቀቅ የቦታውን አዲስ ክብረወሰን አስመዝግቧል። አትሌቱ ባለፈው ዓመት በተካሄደው የሲድኒ ማራቶን 2ኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ የሚታወስ ሲሆን፣ ዘንድሮ ግን የቦታውን ክብረወሰን ከአንድ ደቂቃ በላይ አሻሽሏል። አትሌት ጭምዴሳ ደበሌ 2:04:46 በሆነ ጊዜ 2ኛ ደረጃን ይዞ ሲያጠናቅቅ፣ ጀማል መኮንን 5ኛ ደረጃን አግኝቷል። የባለፈው ዓመት አሸናፊና የቦታው ክብረወሰን ባለቤት የነበረው ኃይለማሪያም ኪሮስ 6ኛ ዳዊት ወልዴ 8ኛ ወጥተዋል። በሴቶች ኬንያዊቷ አትሌት ፔሬስ ጄፕቺርቺር በ2:18:31 በማጠናቀቅ ቀዳሚ ሆናለች። ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች ሹሬ ደምሴ፣ ሄቨን ኃይሉ እና መሰረት አበባየሁ ከ3ኛ እስከ 5ኛ ያሉትን ደረጃዎች በመያዝ ውድድራቸውን አጠናቀዋል።
የፕሪሚየር ሊጉ ተጠባቂ መርሐ ግብሮች፡ ማንችስተር ዩናይትድ ከኢፕስዊች ታውን፣ ቼልሲ ከብራይተን
Aug 30, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬም ቀጥለው ይካሄዳሉ። በዕለቱ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከመርሐ ግብሮቹ መካከል ማንችስተር ዩናይትድ ከኤፕስዊች ታውን ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ላይ በኦልትራፎርድ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠቃሽ ነው። ዩናይትድ በመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር ባልተጠበቀ ሁኔታ በአዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ 2 ለ 0 ተሸንፏል። በአንጻሩ አዲስ አዳጊው ኤፕስዊች ታውን ሰንደርላንድን 2 ለ 1 በማሸነፍ ዓመቱን በድል ጀምሯል። ማንችስተር ዩናይትድ አሁንም ከአዲስ አዳጊ ክለብ ጋር ተገናኝቷል። ቡድኑ የመጀመሪያ ድሉን ለማግኘት ይጫወታል። ኤፕስዊች ታውን ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ጠንካራ ፍልሚያ ይጠብቀዋል።   በሌላኛው መርሐ ግብር ቼልሲ ብራይተንን ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ያስተናግዳል። የምዕራብ ለንደኑ ቼልሲ በመጀመሪያው ጨዋታው ከሜዳው ውጪ ፉልሃምን 2 ለ 1 ረቷል። የምስራቅ ኤሴክሱ ብራይተን አስቶንቪላን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። በመጀመሪያ መርሐ ግብራቸው ድንቅ የማጥቃት እንቅስቃሴ ያሳዩት ሁለቱ ቡድኖች ዛሬም ማራኪ ጨዋታ ለተመልካች እንደሚያሳዩ ይጠበቃል። ሊድስ ዩናይትድ ከብሬንትፎርድ፣ ሰንደርላንድ ከፉልሃም በተመሳሳይ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ቶተንሃም ሆትስፐርስ ተከታታይ ሽንፈት አስተናገደ
Aug 29, 2026 246
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኒውካስትል ዩናይትድ ቶተንሃም ሆትስፐርስን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በቶተንሃም ሆትስፐርስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶኒ ኢላንጋ እና ዮአን ዊሳ የማሸነፊዬ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኒውካስትል ዩናይትድ ያገኛቸውን የግብ እድሎች በሚገባ መጠቀሙ አሸናፊ አድርጎታል። ባለሜዳው ቶተንሃም የጨዋታ ብልጫ ቢወስድም ኢላማቸውን የጠበቁ ሙከራዎችን ማድረግ ላይ ተቸግሮ ታይቷል። ውጤቱን ተከትሎ ኒውካስትል የውድድር ዓመቱን የመጀመሪያ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። አዲሱ ጀርመናዊ አሰልጣኝ ማቲያስ ጃይስል የመጀመሪያ ድላቸውን አግኝተዋል። በአንጻሩ ቶተንሃም ሆትስፐርስ ተከታታይ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት በርካታ ገንዘብ ያወጣው የሮቤርቶ ዲዘርቢው ቶተንሃም ደካማ አጀማመር አሳይቷል። በሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከኖቲንግሃም ፎረስት፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ከቦርንማውዝ ይጫወታሉ።
አዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ ተከታታይ ድሉን ሲያስመዘግብ ቦርንማውዝ እና ኤቨርተን አቻ ተለያይተዋል
Aug 29, 2026 115
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬም መካሄዱን ቀጥሏል። በኮቨንተሪ ቢውልዲንግ ሶሳይቲ አሬና በተካሄደው ጨዋታ ሁል ሲቲ ኮቨንተሪ ሲቲን 1 ለ 0 አሸንፏል። ሊያም ሚላር በ82ኛው ደቂቃ ግቧን አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ አዲስ አዳጊው ሁልሲቲ ተከታታይ ድሉን በማስመዝገብ ያልተጠበቀ ጅማሮ አድርጓል። በአንጻሩ ሌላኛው አዳጊ ክለብ ኮቨንተሪ ሲቲ ተከታታይ የሊግ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በቫይታሊቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ቦርንማውዝ እና ኤቨርተን አንድ አቻ ተለያይተዋል። አሌክስ ስኮት ለቦርንማውዝ፣ ጀምስ ታርኮስኪ ለኤቨርተን ግቦቹን አስቆጥረዋል። ታርኮስኪ በ91ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ኤቨርተንን አቻ አድርጋለች። በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታቸው ሽንፈት ያስተናገዱት ሁለቱ ክለቦች የመጀመሪያ ነጥባቸውን አግኝተዋል። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከኒውካስትል ዩናይትድ በቶተንሃም ሆትስፐርስ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቀን ላይ በተካሄደ ጨዋታ ሊቨርፑል እና ኖቶንግሃም ፎረስት ሁለት አቻ ተለያይተዋል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በግማሽ ፍጻሜው ሽንፈት አስተናገደ
Aug 29, 2026 137
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ የግማሽ ፍጻሜ መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ 3 ለ 0 ተሸንፏል። በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆቪያ ናካጎሎ፣ አግነስ ናቡኬንያ እና የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ትዕግስት አዳነ በራሷ ላይ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ወክሎ የመሳተፍ ህልሙ ግማሽ ፍጻሜ ላይ ተገቷል። ንግድ ባንክ ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ይጫወታል። የዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ለፍጻሜ አልፏል። በፍጻሜው ከኬንያ ፖሊስ ቡሌትስ እና ከደቡብ ሱዳን ዬ ጆይንት ስታርስ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። ኬንያ ፖሊስ ቡሌትስ እና ዬ ጆይንት ስታርስ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታቸውን በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም ይጫወታሉ። የግማሽ ፍጻሜ አሸናፊ ቡድኖች ሰኞ ነሐሴ 25 ቀን 2018 ዓ.ም በፍጻሜው ይገናኛሉ። የማጣሪያ ውድድሩን የሚያሸንፈው ክለብ በሻምፒዮንስ ሊጉ ሴካፋ ዞንን ወክሎ መሳተፉን ያረጋግጣል። ነሐሴ 15 ቀን 2018 ዓ.ም በሩዋንዳ ኪጋሊ የተጀመረው የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ከነገ በስቲያ ይጠናቀቃል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ለሴካፋ ማጣሪያ ፍጻሜ ለማለፍ ከካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ጋር ይጫወታል
Aug 29, 2026 111
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ጋር የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል። ጨዋታው ከቀኑ ስምንት ሰዓት ላይ በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በምድብ ሁለት በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። በአሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው የሚሰለጥነው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሶስቱ ምድብ ምርጥ ሁለተኛ ሆኖ በማጠናቀቁ ምክንያት ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የጅቡቲውን ኡጄኮን 11 ለ 0 በመርታቱ ባለው የግብ ክፍያ ምርጥ ሁለተኛ ሆኖ እንዲያጠናቅቅ አስችሎታል። ንግድ ባንክ በምድቡ በካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ የ1 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ በምድብ ሁለት በስድስት ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። በምድብ ሁለት አንደኛ ሆኖ ያጠናቀቀው ካዌምፔ እና ምርጥ ሁለተኛ ሆኖ የጨረሰው ንግድ ባንክ ዳግም በግማሽ ፍጻሜው ተገናኝተዋል። ሁለቱ ክለቦች እ.አ.አ በ2024 በአዲስ አበባ በተካሄደው የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ማጣሪያ በግማሽ ፍጻሜ ተገናኝተው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። ንግድ ባንክ በወቅቱ የማጣሪያ ውድድሩን በማሸነፍ በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመጀመሪያ ጊዜ መሳተፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሐ ግብር ኬንያ ፖሊስ ቡሌስ ከደቡብ ሱዳኑ ዬ ጆይንት ስታርስ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም ይጫወታሉ። የግማሽ ፍጻሜ አሸናፊ ቡድኖች ሰኞ ነሐሴ 25 ቀን 2018 ዓ.ም በፍጻሜው ይገናኛሉ። የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ከነሐሴ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በሩዋንዳ ኪጋሊ እየካሄደ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የማጣሪያ ውድድሩን ካሸነፈ በሻምፒዮንስ ሊጉ ለሁለተኛ ጊዜ መሳተፉን ያረጋግጣል። በ2026 የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ ለመሳተፍ 36 ክለቦች በስድስት አህጉራዊ ዞኖች ተከፍለው የማጣሪያ ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል። በአህጉራዊ ቀጣናዎች በሚደረጉ ማጣሪያዎች አሸናፊ የሆኑ ክለቦች፣ የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ የሞሮኮው ኤኤስ ፋር እና ውድድሩን የሚያዘጋጀው ሀገር ተወካይ ጨምሮ ስምንት ቡድኖች በዋናው ውድድር ላይ እንደሚሳተፉ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል። የ2026 የካፍ የሴቶች ቻምፒየንስ ሊግ ዋና ውድድር አዘጋጅ ሀገር በቅርቡ በአወዳዳሪው አካል ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
ሊቨርፑል ከኖቲንግሃም ፎረስት፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ፡- የዕለቱ ተጠባቂ ግጥሚያዎች
Aug 29, 2026 126
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 8 : 30 ላይ ሊቨርፑል ከኖቲንግሃም ፎረስት በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሊቨርፑል በመጀመሪያው የሊጉ ጨዋታ ከኒውካስትል ዩናይትድ ጋር ሁለት አቻ ተለያይቷል። በአንጻሩ ኖቲንግሃም ፎረስት በሜዳው በሊድስ ዩናይትድ የ1 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ሁለቱ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ ከዚህ ቀደም 15 ጊዜ ተገናኝተዋል። ሊቨርፑል በስምንቱ ሲያሸንፍ ፎረስት አራት ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪዎቹ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ሊቨርፑል በ15ቱ ጨዋታዎች ላይ 20 ጎሎችን ሲያስቆጥር ኖቲንግሃም ፎረስት 13 ግቦችን አስቆጥሯል። ባለፉት አምስት የሊግ ግንኙነታቸው ሊቨርፑል ሶስት ጊዜ ድል ሲቀናው ፎረስት አንድ ጨዋታ አሸንፏል። በቀሪው መርሐ ግብር ነጥብ ተጋርተዋል። ሁለቱም ክለቦች ዛሬ የውድድር ዓመቱን የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይፋለማሉ። በሌሎች መርሐ ግብሮች አዲስ አዳጊዎቹ ኮቨንተሪ ሲቲ ከሁል ሲቲ እና ቦርንማውዝ ከኤቨርተን በተመሳሳይ 11 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከኒውካስትል ዩናይትድ ጋር በቶተንሃም ሆትስፐርስ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ባለሜዳው ቶተንሃም በመጀመሪያው ጨዋታ በብሬንትፎርድ የ3 ለ 0 ሽንፈት ሲያስተናግድ ኒውካስትል ከሊቨርፑል ጋር ሁለት አቻ ተለያይቷል። ቡድኖቹ የአዲሱን የውድድር ዓመት የመጀመሪያ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይፋለማሉ።
ማንችስተር ሲቲ ተከታታይ ድሉን አስመዘገበ
Aug 29, 2026 139
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት የመጀመሪያ መርሐ ግብር ማንችስተር ሲቲ ክሪስታል ፓላስን 4 ለ 1 ረትቷል። ማምሻውን በሰልኸረስት ፓርክ ስታዲየም አርሊንግ ሃላንድ እና ራያን ቸርኪ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን አስቆጥረዋል። የማንችስተር ሲቲው ግብ ጠባቂ ጂያንሉዋጂ ዶናሩማ በራሱ ላይ ያስቆጠረው ጎል የፓላስ ግብ ሆኖ ተመዝግቧል። በጨዋታው ብልጫ የወሰደው ማንችስተር ሲቲ ተጨማሪ ግቦችን ማስቆጠር የሚችልባቸውን እድሎች መጠቀም አልቻለም። ባለሜዳው ክሪስታል ፓላስ በቂ የግብ እድሎችን መፍጠር ተስኖታል። ሁለት ግቦችን በማስቆጠር ድንቅ እንቅስቃሴ ያደረገው ራያን ቸርኪ የጨዋታው ኮከብ ተጫዋች በመባል ተመርጧል። በ85 ሚሊዮን ፓውንድ ከሊል ማንችስተር ሲቲን የተቀላቀለው አዩብ ቡአዲ ተቀይሮ በመግባት የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ ተከታታይ ድሉን በማስመዝገብ ሊጉን መምራት ተችሏል። በአንጻሩ የለንደኑ ክለብ ክሪስታል ፓላስ ተከታታይ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በሶስተኛው ሳምንት መርሐ ግብር ክሪስታል ፓላስ ከፉልሃም፣ ማንችስተር ሲቲ ከኮቨንተሪ ሲቲ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የፕሪሚየር ሊጉ የሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር እስከ ነሐሴ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
ማንችስተር ሲቲ ከክሪስታል ፓላስ ጋር ጨዋታውን ያደርጋል
Aug 28, 2026 163
  አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጀመራል። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ክሪስታል ፓላስ ከማንችስተር ሲቲ በሰልኸረስት ፓርክ ይጫወታሉ። በመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር ክሪስታል ፓላስ በኤቨርተን የ2 ለ 0 ተሸንፏል። አዲሱ የፓላስ አሰልጣኝ ፒዬር ሴጅ የአሰልጣኝነት ቆይታቸውን በሽንፈት ጀምረዋል። በአንጻሩ የማንችስተር ሲቲው አዲስ አሰልጣኝ ኤንዞ ማሬስካ በመጀመሪያ ሳምንት ጨዋታ ቡድናቸው ቦርንማውዝን 2 ለ 1 አሸንፏል። ሁለቱ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ ለ33ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 32 ጨዋታዎች ማንችስተር ሲቲ 20 ጊዜ ሲያሸንፍ ክሪስታል ፓላስ አራት ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ ስምንት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ማንችስተር ሲቲ በጨዋታዎቹ 75 ግቦችን ሲያስቆጥር ክሪስታል ፓላስ በበኩሉ 28 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ክሪስታል ፓላስ ለመጨረሻ ጊዜ ሲቲን በሊጉ ያሸነፈው እ.አ.አ በ2021 ነው። ጨዋታው ማንችስተር ሲቲ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ፣ ክሪስታል ፓላስ በአዲሱ የውድድር ዓመቱን የመጀመሪያ ሶስት ነጥቡን ለማግኘት የሚያደርጉት ነው። የ42 ዓመቱ አንዲ ማድሊ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር እስከ ነሐሴ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።  
የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ድልድል ይፋ ሆነ
Aug 27, 2026 766
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 21 /2018(ኢዜአ)፦ የ2026/27 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ድልድል ዛሬ ማምሻውን በሞናኮ ይፋ ሆኗል። ውድድሩ ጳጉሜን 3 ቀን 2018 ዓ.ም ይጀመራል። የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ከ2016 ዓ.ም የውድድር ዓመት አንስቶ ሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ድልድል ፎርማትን በማስቀረት 36 ክለቦች በ4 ቋቶች (Pots) በመከፋፈል እንዲጫወቱ የሚያደርግ አዲስ አሰራር (League Phase) መተግበር መጀመሩ ይታወቃል። በዚሁ መሰረት 36ቱ ቡድኖች በ4 ቋቶች የተደለደሉ ሲሆን በእያንዳንዱ ቋት 9 ክለቦች ይገኛሉ። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ ፣ ሪያል ማድሪድ፣ ባየር ሙኒክ፣ ማንችስተር ሲቲ፣ አርሰናል፣ ባርሴሎና፣ ኢንተር ሚላን፣ ሊቨርፑል እና አትሌቲኮ ማድሪድ ተደልድለዋል። ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ፣ ሮማ ፣ ስፖርቲንግ ሊዝበን ፣ አስቶንቪላ፣ ፓርቶ፣ ማንችስተር ዩናይትድ ፣ ክለብ ብሩዥ፣ ሪያል ቤቲስ እና ፒኤስጂ አይንድሆቨን በቋት ሁለት የሚገኙ ክለቦች ናቸው። በቋት ሶስት ላይፕዚግ፣ ቪያሪያል፣ ናፖሊ፣ ሊል፣ ፌይኖርድ ሮተርዳም፣ ቦዲ ግሊምት፣ ፊነርባቼ፣ ሻካታር ዶኔስክ እና ጋላታሳራይ ላይ ይገኛሉ። ስቱትጋርት፣ ሌንስ፣ ስላቪያ ፕራግ፣ ስሎቫን ብራቲስላቫ ፣ ኤኢኬ አቴንስ ፣ ላስክ፣ ኮሞ፣ ቫይኪንግ እና ሳባህ በቋት አራት የተደለደሉ ክለቦች ናቸው። አንድ ክለብ በራሱ ቋት ካለ ሁለት ቡድንና በእያንዳንዱ ቋት ካሉ ሁለት ክለቦች ጋር ጨዋታውን ያደርጋል። በዚህም አንድ ክለብ ስምንት ጨዋታ ያደርጋል። ከ36 ክለቦች መካከል በስምንት ጨዋታዎች የተሻለ ውጤት ያስመዘገቡ ስምንት ቡድኖች በቀጥታ ወደ ጥሎ ማለፉ ይገባሉ። ቀሪዎቹ ስምንት ወደ ጥሎ ማለፉ የሚገቡ ቡድኖች በሁለት የማጣሪያ ዙሮች ተጫውተው 16ት ውስጥ ይገባሉ። ከጥሎ ማለፉ አንስቶ ያለው የውድድር ፎርማት ከዚህ ቀደም ከነበረው ጋር ተመሳሳይነት ያለው ነው። በዚሁ መሰረት ሪያል ማድሪድ ከአርሰናል፣ ማንቸስተር ሲቲ ከባርሴሎና፣ ማንቸስተር ዩናይትድ ከባየር ሙኒክ ፣ ባርሴሎና ከፒኤስጂ እና ሊቨርፑል ከአትሌቲኮ ማድሪድ በመጀመሪያው ሳምንት ከሚደረጉ ጨዋታዎች መካከል የሚጠበቁ ናቸው። የጣልያኑ ኮሞ እና የአዘርባጃኑ ሳባህ በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚሳተፉ ክለቦች ናቸው።
ማንችስተር ዩናይትድ ለአመታት ሲፈልገው የነበረውን ካርሎስ ባሌባን አስፈረመ
Aug 25, 2026 377
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ማንችስተር ዩናይትድ የካሜሮኑን አማካይ ካርሎስ ባሌባን ከብራይተን በ70 ሚሊዮን ፓውንድ ማስፈረሙን ዛሬ አስታውቋል። የ22 ዓመቱ ተጫዋች በኦልድ ትራፎርድ ለቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የሚያቆየውን ኮንትራት የተፈራረመ ሲሆን፣ እስከ እ.አ.አ 2031 በሚቆየው በዚህ ውል ላይ የክለቡ ተጨማሪ የ12 ወራት የማራዘም አማራጭ ተካቷል። ባሌባ ወደ አዲሱ ክለቡ መቀላቀሉን አስመልክቶ በሰጠው አስተያየት፣ ለረጅም ጊዜ ለመቀላቀል ሳልመው በነበረው ማንችስተር ዩናይትድ መፈረም በመቻሌ ታላቅ ደስታና ክብር ይሰማኛል ብሏል። ከአሰልጣኝ ማይክል ካሪክ ጋር በመስራት እና የእሱን ልምድ በመጠቀም ብቃቱን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ እንደሚፈልግም ገልጿል። ባሌባ በማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ማይክል ካሪክ ስር በክረምቱ የዝውውር መስኮት የፈረመ ሶስተኛው የአማካይ ተጫዋች ሆኗል። ዩናይትድ ቀደም ሲል አንድሬ ሳንቶስን ከቼልሲ በ48 ሚሊዮን ፓውንድ እና ዩሪ ቲሊማንስን ከአስቶንቪላ በ35 ሚሊዮን ፓውንድ ማስፈረሙ ይታወቃል።
ቼልሲ የውድድር ዓመቱን በድል ጀምሯል
Aug 24, 2026 411
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ ግብር ቼልሲ ፉልሃምን 3 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በክራቫን ኮቴጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆአኦ ፔድሮ፣ ሞርጋን ሮጀርስ እና ኮል ፓልመር የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ጆአኦ ፔድሮ በ31ኛው ሴኮንድ ያስቆጠረው የዓመቱ ፈጣን ጎል ሆኖ ተመዝግቧል። ጆሹዋ ኪንግ እና ጎንዛሎ ጋርሺያ የፉልሃምን ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በ117 ሚሊዮን ፓውንድ ከአስቶንቪላ ወደ ቼልሲ የተዘዋወረው ሞርጋን ሮጀርስ በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታው ጎል አስቆጥሯል። ከሪያል ማድሪድ ፉልሃምን የተቀላቀለው ጎንዛሎ ጋርሺያም የመጀመሪያ የሊግ ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው እጅግ አዝናኝና በርካታ የግብ እድሎች የተፈጠሩበት ነበር። የቼልሲው አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ በመጀመሪያ ጨዋታው ድል ቀንቶታል። በአንጻሩ አዲሱ የፉልሃም አዲሱ አሰልጣኝ አርቫሎ አርቤሎአ በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታቸው ሽንፈት አስተናግዷል። ጨዋታውን ተከትሎ የመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር ተጠናቋል። የሁለተኛ ሳምንት የሊጉ ጨዋታዎች ከአርብ ነሐሴ 22 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም