ቀጥታ፡
ስፖርት
ተወዳዳሪ ብሔራዊ ቡድን ለመገንባት በስፖርት መሰረተ ልማትና ታዳጊዎች ላይ መስራት ይገባል
Jul 26, 2026 168
ሀዋሳ፤ሐምሌ 19/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እግር ኳስ ተወዳዳሪና ጠንካራ ብሔራዊ ቡድን ለመገንባት በስፖርት መሠረተ ልማትና ታዳጊዎች ላይ የሚሰሩ ስራዎች ሊጠናከሩ እንደሚገባ ተጠቆመ። እ.አ.አ. በ1957 የተመሰረተው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) መስራች ከነበሩ ሀገራት አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ ለአፍሪካ እግር ኳስ ዕድገት ትልቅ አሻራ አሳርፋለች። የአፍሪካ እግር ኳስ በዓለም መድረክ የሚገባውን ቦታ እንዲይዝ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረጉት የካፍ ፕሬዝዳንት የነበሩት የይድነቃቸው ተሰማ ሀገር ኢትዮጵያ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የእግር ኳስ አፍቃሪያን ያሉባትም ናት። ኢትዮጵያ ለአፍሪካ እግር ኳስ ዕድገት ያኖረችውን አሻራና የቀደመ ገናና ታሪክ በማንሳት የ2029 የአፍሪካ ዋንጫን ለማስተናገድ ጥያቄ ማቅረቧም ይታወቃል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ክለብ ዋና አሰልጣኝ ያሬድ ገመቹ እና የክለቡ ተጫዋች ሁሴን ጠሃ፤ በኢትዮጵያ ተወዳዳሪ ብሔራዊ ቡድን ለመገንባት በመሰረተ ልማትና ታዳጊዎች ላይ ሊሰራ ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ በእግር ኳሱ የላቀ ችሎታ ያላቸው ተጫዋቾች እንዳሏት አንስተው ተወዳዳሪ ብሔራዊ ቡድን ለመገንባት ዕድሎችን ለመጠቀም ብዙ ልንሰራ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። የ2018ቱ የሲቢኢ ፕሪሚየር ሊግ አሸናፊው ቡድን አሰልጣኝ ያሬድ ገመቹ እንደገለጸው፤ ጠንካራ ብሔራዊ ቡድን ለመገንባት ሌላው ዓለም የሚሰራውን መስራት መቻል አለብን ። የስፖርት መሰረተ ልማትና የታዳጊ ስልጠና ማዕከላትን ማጠናከር፤ የምልመላ ስርዓትና የውድድር ዕድሎችን ማስፋት ቀዳሚዎች መሆናቸውን አንስቷል። ዕምቅ ችሎታ ያላቸው ተጫዋቾች የሚፈሩባቸው ትምህርት ቤቶችን ጨምሮ የሚደረጉ ስልጠናዎችና ውድድሮች ላይ ማተኮር እንደሚገባም አክሏል። አሰልጣኞችን ልምድ ባላቸው ሀገራት ማስተማር፣ ወጥ የሆነ የስልጠና ማኑዋል ማዘጋጀትና ሳይንሳዊ የሆነ የምልመላ ስርዓት መዘርጋት ሌላው ሊተኮርበት የሚገባ ጉዳይ መሆኑን አንስቷል። መንግስት የ2029 የአፍሪካ ዋንጫን ለማስተናገድ ጥያቄ ማቅረቡ በስፖርቱ ዘርፍ ከፍተኛ የሆነ መነሳሳትን እንደሚፈጥር የጠቀሰው አሰልጣኝ ያሬድ ዕድሉን መጠቀም ይገባናል ሲል ገልጿል። ለዋናው ብሔራዊ ቡድን የመጫወት ህልም ይዞ እየሰራ ያለው የክለቡ ከ20 ዓመት በታች የግራ መስመር አጥቂ ሁሴን ጠሃ በበኩሉ፤ ተፎካካሪ ብሔራዊ ቡድን ለመፍጠር ታዳጊዎችና የስልጠና ሜዳዎች ሊጠናከሩ ይገባል ነው ያለው።
የዓለም አትሌቲክስ የአትሌት ትዕግስት አሰፋ የሴቶች ብቻ የማራቶን የዓለም ክብረ ወሰንን አፀደቀ 
Jul 23, 2026 262
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም አትሌቲክስ የኢትዮጵያዊቷ አትሌት ትዕግስት አሰፋ የሴቶች ብቻ (women’s only) የማራቶን የዓለም ክብረ ወሰንን ዛሬ ማፅደቁን ይፋ አድርጓል። አትሌት ትዕግስት እ.አ.አ አፕሪል 26 / 2026 በለንደን ማራቶን 2 ሰዓት ከ15 ደቂቃ ከ41 ሴኮንድ በመግባት እ.አ.አ በ2025 በራሷ ተይዞ የነበረውን ክብረ ወሰን በዘጠኝ ሴኮንድ በማሻሻል አሸንፋለች። የዓለም አትሌቲክስ የአትሌቷን የሴቶች ብቻ የዓለም ክብረ ወሰን ዛሬ ማፅደቁን አስታውቋል። የሴቶች ብቻ (women’s only) የዓለም ክብረ ወሰን ሴቶች ብቻ በሮጡበት ውድድር ብቻ የተመዘገበ የዓለም ፈጣን ሰዓት ማለት ነው። የዚህ የዓለም ክብረ ወሰን አመዘጋገብ በሴቶች ውድድር ላይ የወንድ አሯሯጮች ወይም ወንዶች ተቀላቅለው ሲሮጡ (አጠቃላይ ሩጫ) ከሚመዘገበው የዓለም ክብረ ወሰን ጋር የሚለያይ ነው። ወንዶች በሴቶች ውድድር ላይ መኖራቸው የውድድሩን አዝማሚያ እና ሴቶች የሚያስመዘግቡት ሰዓት ላይ ተጽእኖ እንደሚያሳድር የዓለም አትሌቲክስ አስታውቋል። ሴት እና ወንድ ተደባልቀው በሚሮጡበት አጠቃላይ የሴቶች ማራቶን ውድድር የዓለም ክብረ ወሰንን (Overall women's world record) የያዘችው ኬንያዊቷ አትሌት ሩት ቼፕጌቲች ናት። ሩት እ.አ.አ በ2024 በቺካጎ ማራቶን 2 ሰዓት ከ9 ደቂቃ ከ56 ሴኮንድ በመግባት ክብረ ወሰኑን ጨብጣለች። የዓለም አትሌቲክስ ከአትሌት ትዕግስት በተጨማሪ ሰባት የዓለም ክብረ ወሰኖችን ማጽደቁን አስታውቋል። እውቅናና ፈቃድ በተሰጣቸው ውድድሮች ላይ ማሸነፍ፣ የውድድር ሜዳዎቹ የሚፈለገውን መስፈርት ያሟሉ መሆንና አትሌቶች በአበረታች ቅመም ምርምራ ውጤት ጤነኛ መሆናቸው መረጋገጥ አትሌቶች የዓለም ክብረ-ወሰን ባለቤት የሚሆኑባቸው ዋነኛ ቅደመ-ሁኔታዎች ናቸው።
ስፔን አርጀንቲናን በመርታት የዓለም ዋንጫን አነሳች
Jul 20, 2026 505
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የፍጻሜ መርሐ ግብር ስፔን አርጀንቲናን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በኒው ዮርክ ኒው ጀርዚ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ግብ ሳይቆጠርበት በአቻ ውጤት ተጠናቋል። የአርጀንቲና የአማካይ ተጫዋች ኤንዞ ፈርናንዴዝ በ93ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። በ90 ደቂቃ አሸናፊ ባለመገኘቱ ቡድኖቹ ወደ ጭማሪ ሰዓት አምርቷል። ተቀይሮ የገባው ፌራን ቶሬስ በ106ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ስፔን ፍጹም የበላይነት ወስዳለች። የአርጀንቲናው ግብ ጠባቂ ኤሚሊያኖ ማርቲኔዝ በርካታ ያለቀላቸው ኳሶችን አድኗል። ተጋጣሚዋ አርጀንቲና በጨዋታው ደካማ እንቅስቃሴ አድርጋለች። ቡድኑ የግብ እድል መፍጠር ተስኖታል። ውጤቱን ተከትሎ ስፔን ለሁለተኛው የዓለም ዋንጫን አንስታለች። አውሮፓዊቷ ሀገር እ.አ.አ በ2010 ደቡብ አፍሪካ ባዘጋጀችው 19ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ አሸናፊ እንደነበረች ይታወሳል። አርጀንቲና የዓለም ዋንጫ ክብሯን ማስጠበቅ አልቻለችም። ለአራተኛ ጊዜ ዋንጫ የማንሳት ህልሟ አልተሳካም።
“ልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክ” ታላቁ ሩጫ በሐረር ከተማ ተካሄደ
Jul 19, 2026 378
ሀረር ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ “ልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክ 2018” የ10 ኪሎ ሜትር ታላቁ ሩጫ ውድድር በሐረር ከተማ ተካሄደ። በውድድሩ በተለያየ የዕድሜ ክልል ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎች፣ አትሌቶች፣ ተጋባዥ እንግዶች፣ የውጪ አገር ቱሪስቶች፣ አርቲስቶችን ጨምሮ በርካታ ነዋሪዎች ተሳታፊ ሆነዋል። ልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክ የሩጫ ውድድር ቀደም ሲል በደብረብርሃን፣ ሀዋሳ፣ ጅማ፣ አርባ ምንጭና በቆጂ ከተሞች የተካሄደ ሲሆን የፍጻሜ ውድድሩ ዛሬ በሐረር ከተማ ተካሂዷል።   በታሪካዊቷ ሐረር ከተማ በተካሄደው የታላቁ ሩጫ ውድድርን የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሀመድና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተው አስጀምረዋል። በ10 ኪሎ ሜትር በተካሄደው በዚህ ውድድር በወንዶች ሴና ገመቹ ሲያሸንፍ፤ ምህረት አወቀና ኢብራሂም መሀመድ በቅደም ተከተል 2ኛ እና 3ኛ ደረጃን በመያዝ ውድድሩን አጠናቀዋል። በሴቶች ራሔል እምቢበል ስታሸንፍ አምረን ሸምሱና አዚዛ መሀመድ ሁለተኛ እና ሦስተኛ ደረጃን አግኝተዋል።   በሁለቱም ጾታ ከተደረገው የአትሌቶች ውድድር በተጨማሪ በአዋቂዎች፣ በወጣቶች፣ በታዳጊ ሕጻናትና በሌሎች ተጋባዥ እንግዶች በሁለቱም ጾታዎች የ5 ኪሎ ሜትር ውድድር ተከሂዷል። ውድድሩን ላሸነፉ ተወዳዳሪዎች የተዘጋጀላቸውን የማበረታቻ ሽልማት ከእለቱ የክብር እንግዳ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ፣ ከባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሀመድ አበርክተዋል።   “ልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክ 2018” ታላቁ ሩጫ ውድድር ቱሪዝም ሚኒስቴር እና ታላቁ ሩጫ በኢትዮዽያ በመተባበር ያዘጋጁት የጎዳና ላይ ውድድር መሆኑ ተገልጿል። ውድድሩ በሕዝቦች መካከል አብሮነትን የማጠናከር፣ የሀገር ውስጥ ቱሪዝምን የማሳደግ እንዲሁም አዲስ የስፖርት መነቃቃትን የመፍጠር ዓላማ እንዳለውም ተመላክቷል።
አርጀንቲና የዓለም ዋንጫ ክብሯን ታስጠብቃለች ወይስ ስፔን ከ16 ዓመታት በኋላ ዳግም አሸናፊ ትሆናለች?
Jul 19, 2026 607
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የፍጻሜ መርሐ ግብር ስፔን እና አርጀንቲና ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ የዓለም አይኖች አርፈውበታል። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በኒው ዮርክ ኒው ጀርዚ ስታዲየም ይካሄዳል። ስፔን በግማሽ ፍጻሜው ለዋንጫ ታልፋለች ተብላ የተጠበቀችውን ፈረንሳይን 2 ለ 0 በመርታት በታሪኳ ለሁለተኛ ጊዜ ለፍጻሜ ቀርባለች። የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት አርጀንቲና እንግሊዝን 2 ለ 1 በማሸነፍ ለተከታታይ ሁለት የዓለም ዋንጫዎች ለፍጻሜ ደርሳለች። አርጀንቲና ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ ስታልፍ የአሁኑ ለሰባተኛ ጊዜ ነው። ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም በዓለም ዋንጫው አንድ ጊዜ ተገናኝተዋል። እንግሊዝ እ.አ.አ በ1966 ባዘጋጀችው ስምንተኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በምድብ ሁለት ተገናኝተው አርጀንቲና 2 ለ 1 አሸንፋለች። ሉዊስ አርቲም ለአርጀንቲና ሁለቱን ግቦች አስቆጥሯል። ፒሪ የስፔንን ጎል በወቅቱ ያስቆጠረ ተጫዋች ነው። ሀገራቱ በውድድር እና ወዳጅነት ጨዋታዎች 14 ጊዜ ተጫውተው በተመሳሳይ ስድስት ጊዜ ድል ቀንቷቸዋል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ስፔን በ14ቱ ጨዋታዎች ላይ 22 ግቦችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ አርጀንቲና 18 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፋለች። እ.አ.አ በ2018 በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው 19ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ስፔን ብቸኛ ክብሯን ያገኘችበት ነው። ተጋጣሚዋ አርጀንቲና ከዚህ ቀደም ስድስት ጊዜ ለፍጻሜ ደርሳ ሶስቱን በማሸነፍ በውድድሩ ስኬታ ከሚባሉ ሀገራት መካከል አንዷ ናት። አርጀንቲና የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፈች ከጀርመን እና ጣልያን ጋር በተመሳሳይ አራት ጊዜ የዓለም ዋንጫን ያነሳች ሀገር ትሆናለች። በተጨማሪም የደቡብ አሜሪካ ሀገር ከጣልያን እና ብራዚል በመቀጠል ዓለም ዋንጫን በተከታታይ ያነሳች ሀገር ለመሆን ትጫወታለች። ሌላኛው ትኩረት የሳበው ጉዳይ ሀገራቱ የየአህጉራቸው ውድድሮች የወቅቱ አሸናፊ መሆናቸው ነው። ስፔን የአውሮፓ ዋንጫ፣ አርጀንቲና የኮፓ አሜሪካ አሸናፊ ናቸው። የአውሮፓ እና የደቡብ አሜሪካ ቁንጮዎች የሚያደርጉት ፍልሚያ ትኩረትን ስቧል። አውሮፓዊቷ ስፔን እ.አ.አ በ2010 የዓለም ዋንጫን ከማንሳቷ በፊት የ2008 የአውሮፓ ዋንጫ አሸናፊ ነበረች። ስፔን የወቅቱ የአውሮፓ ዋንጫ ባለቤት ሆና ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ መቅረቧ ገጠመኙን የተለየ አድርጎታል። በዘንድሮው ዓለም ዋንጫ ድንቅ ብቃቱን እያሳየ የሚገኘው ሊዮኔል ሜሲ በዛሬው ጨዋታ ልዩ ትኩረት አግኝቷል። የ39 ዓመቱ ሜሲ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ስምንት ጎሎችን በማስቆጠር እና አራት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል ከኪሊያን እምባፔ (10 ጎሎች ሲያስቆጥር እና አራት የግብ እድሎችን ፈጥሯል) በኮከብ ግብ አግቢነቱ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በዓለም ዋንጫው 21 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ በምንጊዜውም የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት ዝርዝር ውስጥ በእምባፔ አንድ ጎል ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ሜሲ ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ ለማጠናቀቅ እና የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን መሪነት ይዞ ለመቀጠል ሁለት ግቦችን ማስቆጠር እና ለግብ የሚሆን ኳስ ማቀበል ይጠበቅበታል። አርጀንቲናዊው ኮከብ በዓለም ዋንጫ በርካታ ጨዋታዎችን በማድረግ (33) እና በርካታ ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል (12) የክብረ ወሰን ባለቤት ነው። እድሜው በገፋበት ሰዓት እያሳየ ያለው ብቃት አድናቆት እንዲጎርፍለት አድርጓል። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ አንድ ግብ ያስቆጠረው የ18 ዓመቱ ላሚን ያማል ከስፔን በኩል ትኩረት የተሰጠው ተጫዋች ነው። ስፔን በጨዋታው ላይ የኳስ ቁጥጥርን መሰረት ያደረገ እና የክንፍ መስመር የማጥቃት እንቅሰቃሴ ላይ ያተኮረ የአጨዋወት ስልት ወደ ሜዳ ይዛ ትገባለች ተብሎ ይጠበቃል። ተጋጣሚዋ አርጀንቲና የተደራጀ የመከላከል ቅርጽ በመያዝ ኳስ ሲያገኙ በፈጣን መልሶ ማጥቃት ግብ የማስቆጠር አጨዋወትን ትከተላለች ተብሎ ይጠበቃል። ጨዋታው ጠንካራ እና በታክቲክ የታጠረ እንደሚሆን ይጠበቃል። የ46 ዓመቱ ስሎቬኒያዊ ስላቫኮ ቪንቺች ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። አሸናፊው ሀገር ከዋንጫው በተጨማሪ የ50 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ያገኛል። ሁለተኛ የሚወጣው ቡድን የ33 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ይበረከትለታል። የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) አጠቃላይ በውድድሩ ላይ ለተሳተፉ ሀገራት የ871 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት አዘጋጅቷል።   አሜሪካዊው ዝነኛ ድምጻዊና ራፐር ፖስት ማሎን (Post Malone) የዓለም ዋንጫው የመዝጊያ ስነ ስርዓት ዋና አቅራቢ (Headline Performer) ነው። ከእሱ በተጨማሪ ሮቢ ዊሊያምስ፣ ኒኮል ሸርዚንገር እና ላውራ ፓውሲኒ የተባሉ ታዋቂ ድምጻውያን እንዲሁም ታዋቂው ዩቲዩበር አይሾው ስፒድ (IShowSpeed) በዝግጅቱ ላይ የሚሳተፉ ሲሆን፣ የሆሊውድ ተዋናዩ ቶም ክሩዝም ልዩ እንግዳ ሆኖ ይቀርባል። በእረፍት ሰዓት (Halftime Show) ላይ ደግሞ ማዶና፣ ሻኪራ፣ ጀስቲን ቢበር፣ ቢቲኤስ (BTS) እና በርና ቦይ ከኮልድ ፕለይ (Coldplay) ጋር በመሆን በውድድሩ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በሚቀርበው የእረፍት ሰዓት ትዕይንት ላይ ስራዎቻቸውን ያቀርባሉ። በአሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ ጣምራ አዘጋጅነት ከሰኔ 4 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ሲካሄድ የቆየው 23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ዛሬ ፍጻሜውን ያገኛል።
እንግሊዝ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ስታጠናቀቅ ኪሊያን ምባፔ አዲስ የዓለም ዋንጫ ክብረ ወሰን አስመዝግቧል
Jul 19, 2026 484
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 11/2018 (ኢዜአ)፦ 10 ጎሎች በተቆጠሩበት የ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የደረጃ ጨዋታ እንግሊዝ ፈረንሳይን 6 ለ 4 አሸንፋለች። ከእኩለ ሌሊት በኋላ በሚያሚ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቡካዮ ሳካ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ሳካ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ሀትሪክ የሰራ አራተኛው ተጫዋች ሆኗል። ዴክላን ራይስ ኢዝሪ ኮንሳ እና ጁድ ቤሊንግሃም ቀሪዎቹን ጎሎች ለሶስቱ አናብስቶች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ኪሊያን ምባፔ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ብራድሊ ብራኮላ እና ኡስማን ዴምቤሌ ቀዎቹን ጎሎች ለሰማያዊዎቹ አስቆጥረዋል። እንግሊዝ በመጀመሪያው አጋማሽ፣ ፈረንሳይ በሁለተኛው አጋማሽ ብልጫ ወስደዋል። በመጀመሪያ አጋማሽ እንግሊዝ 4 ለ 0 እየመራች ብትወጣም ፈረንሳይ ከእረፍት መልስ አራት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ፈረንሳይ ልታሻንፋባቸው የምትችልባቸውን የግብ እድሎች አምክናለች። ጨዋታው በማጥቃት የታጀበ መሆኑንና የቡድኖቹ የላላ የመከላከል እንቅስቃሴ በርካታ ግቦች እንዲቆጠሩ አድርጓል። ጨዋታው አስገራሚ እንቅስቃሴ ተደርጎበታል። የሁለቱ ቡድኖች መርሐ ግብር በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ በርካታ ግቦች የተቆጠሩበት ጨዋታ ሆኗል። በዓለም ዋንጫ የደረጃ ጨዋታ ታሪክ በርካታ ግቦች የተቆጠሩበትም ሆኗል። የ27 ዓመቱ ኪሊያን እምባፔ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ 10 ከፍ በማድረግ የኮከብ አስቆጣሪነቱን መምራት ጀምሯል። ለግብ አመቻችቶ ያቀበላቸውን ኳሶች ብዛት አራት አድርሷል። ከአርጀንቲናዊው ሊዮኔል ሜሲ ጋር ያለውን የግብ ልዩነት ወደ ሁለት ከፍ በማድረግ የወርቅ ጫማውን የመውሰድ እድሉን አስፍቷል። በተጨማሪም በአጠቃላይ በዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች 22 በማድረስ የምንጊዜም ከፍተኛ አስቆጣሪነቱን ከሜሲ (21) ተረክቧል። ለሀገሩ 66 ጎሎችን አስቆጥሯል። የፈረንሳዩ ማይክል ኦሊሴ በአንድ የዓለም ዋንጫ ሰባት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል የፔሌን (ስድስት የግብ እድል የመፍጠር) ክብረ ወሰንን ሰብሯል። የ23 ዓመቱ ጁድ ቤሊንግሃም በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ሰባት ጎሎችን በማስቆጠር በውድድሩ በአንድ የዓለም ዋንጫ በርካታ ግቦችን ያስቆጠረ እንግሊዛዊ ተጫዋች ሆኗል። ውጤቱን ተከትሎ እንግሊዝ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቅ የነሐስ ሜዳሊያ ባለቤት ሆናለች። እንግሊዝ እ.አ.አ በ1966 አዘጋጅታ ራሷ ካስቀረችው ስምንተኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በኋላ በውድድሩ የተሻለ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ለዋንጫ የተጠበቀችው ፈረንሳይ አራተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። የሁለት ጊዜ ዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ፈረንሳይ አራተኛ ሆኖ ማጠናቀቅ ያልተጠበቀ ሆኗል። ለ14 ዓመት የፈረንሳይ ብሔራዊ ቡድንን ያሰለጠኑት የ57 ዓመቱ ዲዲየር ዴሾ የመጨረሻ ጨዋታቸውን አድርገዋል። ዴሾ በ187 ጨዋታዎች ፈረንሳይ የመሩ ሲሆን አንድ ጊዜ የዓለም ዋንጫን አንስተዋል። ቡድኑን ለሶስት ተከታታይ ዓለም ዋንጫዎች ለፍጻሜ ያበቁ ስኬታማ አሰልጣኝም ናቸው። ዚነዲን ዚዳን በቀጣይ ቡድኑን በአሰልጣኝነት ይረከባል።
በአዲስ አበባ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ታዳጊዎች የክረምት ወራትን በክህሎት ማጎልበቻ እንዲያሳልፉ ዕድል ፈጥረዋል
Jul 18, 2026 283
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 11/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎች የክረምት ጊዜያቸውን በአግባቡ በመጠቀም ተሰጥኦዋቸውን ለማዳበር ትልቅ እድል እንደፈጠረላቸው ታዳጊዎች ገለጹ። መንግስት ለስፖርት ልማት ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን በየደረጃው በመገንባት ለአገልግሎት አብቅቷል፡፡ በአዲስ አበባ ብቁና ተወዳዳሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ውጤታማ የስፖርት ማዕከላትና የማዘውተሪያ ስፍራዎች ተገንብተዋል።   በተገነቡት ከ2ሺህ 580 በላይ የስፖርት ማዘውተሪያና ማሰልጠኛ ማዕከላት ብቃት ያላቸውን ታዳጊ ስፖርተኞች ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑም ተመላክቷል፡፡ እነኚህ ዘመናዊና ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ማዘውተሪያዎች ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን የምታስተናግድበት አቅም መፍጠራቸውም ተገልጿል፡፡ በመዲናዋ በርካታ የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎች መስፋፋታቸው ወጣቶችና ታዳጊዎች በተሻለ ስብዕና እንዲገነቡ የሚያስችሉ ብሎም አልባሌ ቦታዎች ከመዋል የታደጉ ናቸው፡፡ ኢዜአ በአዲስ አበባ በተገነቡ የተለያዩ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ተዘዋውሮ ያነጋገራቸው ታዳጊዎች ከዚህ ቀደም በአካባቢያቸው ምቹ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ባለመኖራቸው ለስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች ይቸገሩ እንደነበር ይናገራሉ። ታዳጊ እያብ ገብረስላሴ እንደሚለው፣ ቀደም ሲል በአካባቢው የነበሩት ሜዳዎች ለስፖርት እንቅስቃሴ አመቺ ስላልነበሩ ተሰጥዖውን ለማዳበር ተቸግሮ እንደነበር ይናገራል። አሁን ላይ በመዲናዋ በተለያዩ አካባቢዎች የተገነቡት ዘመናዊ የስፖርት ማዘውተሪያዎች፣ ታዳጊዎች ተሰጧቸውን በነፃነት የሚያዳብሩበትና ብቃታቸውን የሚያሳድጉበት ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውን ይገልጻል።   ታዳጊ አብርሃም ታረቀኝ እና አማኑኤል ተስፋ በበኩላቸው፣ ቀደም ሲል የነበሩት ሜዳዎች ለጉዳት ይዳርጉ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ግን መንግስት ምቹ ሜዳዎችን በመገንባቱ ያለምንም ስጋት በመለማመድ አቅማቸውን እየገነቡ እንደሚገኙ ገልጸዋል።   ሜዳዎቹ በክረምትም ሆነ በበጋ እንዲሁም ምሽትን ጨምሮ አገልግሎት የሚሰጡ በመሆናቸው ለስፖርታዊ እንቅስቃሴ ትልቅ ሚና እንዳላቸውም ተናግረዋል፡፡ የታዳጊዎች አሰልጣኝ የሆኑት ዮናስ እስክንድር፣ በመዲናዋ የተገነቡት የስፖርት ማዘውተሪያዎች ለታዳጊዎች የመዝናኛና የክህሎት ማሳደጊያ ምቹ መድረክ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በተለይም በክረምት ወራት ተማሪዎች ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ በማስቻል፣ በስፖርት የታነጸ ጤናማ ትውልድ ለመቅረጽ ትልቅ ፋይዳ እንዳላቸው አስረድተዋል። የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ የስፖርት ስልጠና ዳይሬክተር ጎሳዬ አለማየው፣ መንግስት ባለፉት ዓመታት የስፖርት ዘርፉን ለማሳደግ ዘርፈ ብዙ ተግባራት ማከናወኑን አስታውቀዋል። በመዲናዋ በተገነቡት ዘመናዊ የስፖርት ማዘውተሪያዎች አማካኝነትም፣ ታዳጊዎች ክህሎታቸውን አዳብረው በስፖርት የታነጹ እንዲሆኑ ትልቅ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   በዘንድሮ የክረምት ወራት ከ67 ሺህ በላይ ታዳጊዎችን በበጎ ፈቃድ በማሰልጠን ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙና መሰረታዊ የስፖርት ክህሎት እንዲወስዱ እየተደረገ መሆኑንም ገልጸዋል። በስልጠናው ወቅት ከፍተኛ ክህሎት ያሳዩ ታዳጊዎች ወደ በጋው የታዳጊ ወጣት መርሃ ግብር እንዲቀላቀሉ እንደሚደረግ ጨምረው ተናግረዋል።
በዓለም ዋንጫው ማን ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቅቃል? ፈረንሳይ ወይስ እንግሊዝ?
Jul 18, 2026 250
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ፈረንሳይ እና እንግሊዝ ሶስተኛ ደረጃ ይዞ ለመጨረስ ዛሬ ይጫወታሉ። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ላይ በሚያሚ ስታዲየም ይከናወናል። በግማሽ ፍጻሜው ፈረንሳይ በስፔን የ2 ለ 0፣ እንግሊዝ በአርጀንቲና የ2 ለ 1 ሽንፈት አስተናግደዋል። ዓለም ዋንጫውን ታነሳለች ተብላ ተጠብቃ የነበረቸው ፈረንሳይ በስፔን ያስተናገደችው ሽንፈት እና ያሳየችው አቋም ያልተጠበቀ ሆኗል። እንግሊዝ በግማሽ ፍጻሜው እስከ ጨዋታው መገባዳጃ ድረስ 1 ለ 0 እየመራች ብትቆይም በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች የተቆጠሩባት ጎሎች ፍጻሜ የመድረስ ህልሟ እንዳይሳካ አድርጎታል። ሁለቱ ሀገራት ለተመኙት የፍጻሜ ጨዋታ ባይደርሱም ውድደሩን ሶስተኛ ደረጃን ይዘው ለማጠናቀቅ ይፋለማሉ። ብሔራዊ ቡድኖቹ በዓለም ዋንጫው እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። እንግሊዝ እ.አ.አ በ1966 ባሰናዳችው ስምንተኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በምድብ መርሐ ግብት ተገናኝተው አዘጋጇ ሀገር 2 ለ 0 አሸንፋለች። በወቅቱ እንግሊዝ ዋንጫውን በማንሳት ብቸኛ የመድረኩ ክብሯን አግኝታለች። እ.አ.አ በ1982 በስፔን በተካሄደው 12ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በድጋሚ በምድብ ደረጃ ተገናኝተው እንግሊዝ 3 ለ 1 አሸንፋለች። ኳታር እ.አ.አ በ2022 ባዘጋጀችው 22ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በሩብ ፍጻሜው ባደረጉት ጨዋታ ፈረንሳይ 2 ለ 1 በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ፈረንሳይ በውድድሩ ለፍጻሜ ብትደርስም በአርጀንቲና ተሸንፋለች። ሁለቱ ሀገራት የዓለም ዋንጫውን ጨምሮ በውድድር እና በወዳጅነት ጨዋታዎች 32 ጊዜ ተገናኝተዋል። እንግሊዝ 17ቱን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዛለች። ፈረንሳይ በ10ሩ ድል ሲቀናት በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በ32ቱ ጨዋታዎች ላይ እንግሊዝ 72፣ ፈረንሳይ 41 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ፈረንሳይ ለዓለም ዋንጫው ባታልፍም በዘንድሮው ውድድር ድንቅ ብቃቱን ያሳየው የ27 ዓመቱ ኪሊያን እምባፔ በጨዋታው ይጠበቃል። ምባፔ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ስምንት ጎሎችን በማስቆጠር እና ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል ከአርጀንቲናው ሊዮኔል ሜሲ ጋር በጎል እኩል ሆኑ ብዙ ኳስ ባቀበለ በሚለው መለያ (በአንድ ተበልጦ) በኮከብ ግብ አስቆጣሪነቱ ፉክክር ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በአጠቃላይ በውድድሩ ላይ 20 ጎሎች ከመረብ ላይ በማሳረፍ በምንጊዜም ከፍተኛ አስቆጣሪነት ዝርዝር ከሜሲ (21 ጎል) በአንድ አንሶ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ምባፔ በዓለም ዋንጫው የጥሎ ማለፍ ምዕራፍ 12 ጎሎችን በማስቆጠር በውድድሩ አዲስ ክብረ ወሰን አስመዝግቧል። ፈረንሳዊው አጥቂ በዛሬው ጨዋታ ግቦች ካስቆጠረ ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ የማጠናቀቅ እድል ይኖረዋል። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ አምስት ጎሎችን ከመረብ ላይ ያሳረፈው ኡስማን ዴምቤሌ እና አምስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን ያቀበለው ማይክል ኦሊሴም ልዩነት ፈጣሪ ተጫዋቾች ናቸው። ከእንግሊዝ በኩል በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ በተመሳሳይ ስድስት ግቦችን ያስቆጠሩት ጁድ ቤሊንግሃም እና ሃሪ ኬን ይጠበቃሉ። ሁለቱ ተጫዋቾች በኮከብ ግብ አስቆጣሪነቱ ተፎካካሪ ናቸው። ፈረንሳይ ከዚህ ቀደም በሁለት የዓለም ዋንጫዎች (እ.አ.አ 1958 እና 1986) ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። እንግሊዝ ከዚህ ሁለት ጊዜ (እ.አ.አ በ1990 እና 2018) ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ለማጠናቀቅ ተጫዋውታ ሽንፈት አስተናግዳለች። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ42 ዓመቱ ቬንዙዌላዊ ጄሱስ ኖኤል ቫለንዝዌላ ሳኤዝ ጨዋታውን በመሐል ዳኝነት እንዲመሩት ተመድበዋል።
አርጀንቲና እንግሊዝን በመርታት ለፍጻሜ አለፈች
Jul 15, 2026 1391
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ መርሐ ግብር አርጀንቲና ከመመራት ተነስታ እንግሊዝን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ማምሻውን በአትላንታ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የ25 ዓመቱ የክንፍ መስመር ተጫዋች አንቶኒ ጎርደን በ55ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል እንግሊዝን መሪ አድርጓል። ሞርጋን ሮጀርስ ኳሷን አመቻችቶ አቀብሏል። አርጀንቲና ከግቡ መቆጠር በኋላ ተጭና ተጫውታለች። ኤንዞ ፈርናንዴዝ በ85ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል አርጀንቲናን አቻ አድርጓል። ላውታሮ ማርቲኔዝ በ92ኛው ደቂቃ የአርጀንቲናን የማሸነፊያ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። እንግሊዝ መሪነቷን ማስጠበቅ አልቻለችም። ጨዋታው ጉልበት እና ኃይል የተቀላቀለበት ነበር። በርካታ ጥፋቶችም ተሰርተዋል። ሊዮኔል ሜሲ ለ12ኛ ጊዜ በዓለም ዋንጫ ለግብ የሚሆን ኳስ በማቀበል አዲስ ክብረ ወሰን አስመዝግቧል። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ስምንት ጎሎችን አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ አርጀንቲና ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ አልፋለች። የወቅቱ የዓለም ዋንጫ አሸናፊ አርጀንቲና ለስድስተኛ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ ደርሰዋል። አርጀንቲና በፍጻሜው ከስፔን ጋር ትገናኛለች። እንግሊዝ ለሁለተኛ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ የማለፍ ህልሟ አልተሳካም። እንግሊዝ ከፈረንሳይ ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ቅዳሜ ሐምሌ 11 ቀን 2018 ዓ.ም ይጫወታሉ። ስፔን ከአርጀንቲና ዋንጫውን ለማንሳት እሁድ ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም በኒው ዮርክ ኒው ጀርዚ ስታዲየም ይፋለማሉ።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የስፖርት መሰረተ ልማትን በማስፋፋት ብቁ ዜጋ የማፍራት ሥራ ተጠናክሯል 
Jul 15, 2026 612
ወልቂጤ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በክልሉ የስፖርት መሰረተ ልማትን በማስፋፋት በአካልና በአዕምሮ የዳበረ ዜጋን ለማፍራት እየተሰራ መሆኑን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ገለጸ። በወልቂጤ ከተማ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተገኙበት የአካል ብቃት እንቅስቃሴ መርሃ ግብር ተካሄዷል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ሃላፊ አቶ ጌታቸው ሌሊሾ እንደገለጹት፤ በክልሉ የስፖርት ልማትን በማስፋፋት በአካልና በአዕምሮ የዳበረ ጤናማና ብቁ ዜጋ ለማፍራት እየተሰራ ነው።   ለዚህም በየአካባቢው የስፖርት ማዘወተሪያዎችን ከማስፋፋት ባለፈ ስፖርትን ባህሉ ያደረገ ማህበረሰብ ለመፍጠር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተው፣ የዛሬው ስፖርታዊ እንቅስቃሴም የዚሁ አካል ነው ብለዋል። በተለይ ወጣቶች ስፖርትን በማዘወተር ያላቸውን ተሰጥኦ እንዲያጎለብቱ መሰራቱን ገልጸዋል፣ ስፖርታዊ እንቅስቃሴው የእርስ በርስ ትስስርንም ያጠናክራል ብለዋል። የወልቂጤ ከተማ ከንቲባ አቶ ሙራድ ከድር በበኩላቸው፤ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ከጤና ጥቅሙ ባለፈ የዜጎችን የአብሮነት እሴት የሚያጎለብትና በራሱ የሚተማመን ትውልድ ለመቅረጽ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።   ለዚህም ከተማዋ በብስክሌት፣ በቅርጫት ኳስ፣ በእግር ኳስ ጠንካራ ስፖርተኞች ለማፍራት የሚያስችል የስፖርት መሰረተ ልማቶችን እየገነባች መሆኑን አክለዋል። ይህም ለከተማዋ ኢኮኖሚና የስፖርት ቱሪዝም መነቃቃት ጉልህ ድርሻ እየተወጣ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ከተሳታፊዎች መካከል ኢንስፔክተር አብድልሰመድ መሃመድ፤ በከተማዋ የስፖርት ልማቱን የሚያቀላጥፉ መሰረተ ልማቶች መከናወናቸው የሚበረታታ መሆኑን አንስተዋል።   የአካል ብቃት እንቅስቃሴ መርሀግብሩ በስፖርት ጤናማና ብቁ ዜጋ ለመገንባት ለሚደረገው ጥረት አጋዥ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ አቶ ካሚል ጀማል ናቸው።   መርሀግብሩ የእርስ በርስ ግንኙነትን በማጠናከር የበጎ ፈቃድ ሥራዎችን በጋራ ለማከናወን ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸውም ጠቅሰዋል።
ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ ማን ያልፋል? እንግሊዝ ወይስ አርጀንቲና? ተጠባቂው ፍልሚያ!
Jul 15, 2026 776
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ሁለተኛ የግማሽ ፍጻሜ መርሐ ግብር እንግሊዝ ከአርጀንቲና ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በአትላንታ ስታዲየም ይካሄዳል። እንግሊዝ በሩብ ፍጻሜው ኖርዌይን 2 ለ 1 በማሸነፍ የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብታለች። ሶስቱ አናብስቶች ለግማሽ ፍጻሜ ሲያልፉ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። ተጋጣሚዋ አርጀንቲና ስዊዘርላንድን 3 ለ 1 በመርታት ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። የወቅቱ የዓለም ሻምፒዮን አርጀንቲና አራት ውስጥ ስትገባ ለሰባተኛ ጊዜ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። የደቡብ አሜሪካዋ ሀገር ከዚህ ቀደም ያደረጋቻቸውን ስድስት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሙሉ በማሸነፍ ስኬታማ ክብረ ወሰን አላት። እንግሊዝ በበኩሏ ከሶስት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች መካከል ያሸነፈችው አንዱን ብቻ ነው። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫው ከዚህ ቀደም አምስት ጊዜ ተገናኝተዋል። እ.አ.አ በ1962 በቺሊ በተካሄደው ሰባተኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በምድብ አራት ተገናኝተው እንግሊዝ አርጀንቲናን 3 ለ 1 አሸንፋለች። እንግሊዝ እ.አ.አ በ1966 ባዘጋጀችው ስምንተኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ ላይ ተገናኝተው አዘጋጇ ሀገር 1 ለ 0 ያሸነፈች ሲሆን እስከ መጨረሻው በመጓዝ ምዕራብ ጀርመን (በወቅቱ በነበረው ስያሜዋ) በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። በሀገራቱ የዓለም ዋንጫ ግንኙነት ውስጥ ሁሌም የሚታወሰው ጨዋታ እ.አ.አ በሜክሲኮ አዘጋጅነት በተካሄደው 13ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በሩብ ፍጻሜው የተገናኙበት መርሐ ግብር ነው። አርጀንቲና እንግሊዝን 2 ለ 1 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። ዲያጎ ማራዶና ሁለቱንም ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፏል። በወቅቱ ማራዶና በእጁ ያስቆጠራት አወዛጋቢ ጎል “ የፈጣሪ እጅ” (Hand of God) እየተባለች ትጠራለች። አርጀንቲና ፍጻሜ በመድረስ ምዕራብ ጀርመንን (በወቅቱ የነበረው አጠራሯ) በማሸነፍ ዋንጫውን ለሁለተኛ ጊዜ አንስታለች። ፈረንሳይ እ.አ.አ በ1998 ባዘጋጀችው 16ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በሩብ ፍጻሜው መርሐ ግብር 16 ውስጥ ተገናኝተው በጨዋታ ሁለት አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቆ አርጀንቲና በመለያ ምት 4 ለ 3 በማሸነፍ ለሩብ ፍጻሜው አልፋለች። ቡድኖቹ ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተገናኙት ኮሪያ ሪፐብሊክ እና ጃፓን እ.አ.አ በ2002 ባዘጋጁት 17ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ላይ ነበር። በምድብ ስድስት ባደረጉት ጨዋታ እንግሊዝ በዴቪድ ቤካም የፍጹም ቅጣት ምት ጎል 1 ለ 0 አሸንፋለች። ሁለቱ ሀገራት ከ24 ዓመታት በኋላ በመድረኩ ለፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል። ብሔራዊ ቡድኖቹ በውድድር እና ወዳጅነት ጨዋታዎች በአጠቃላይ 14 ጊዜ ተገናኝተው እንግሊዝ ስድስት ጊዜ ድል ሲቀናት አርጀንቲና በሶስቱ ጨዋታዎች አሸንፋለች። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ላይ አቻ ተለያይተዋል። በ14ቱ ጨዋታዎች ላይ እንግሊዝ 21 ጎሎችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ አርጀንቲና 15 ግቦችን አስቆጥራለች። እንግሊዝ የዓለም ዋንጫን አንድ ጊዜ ስታነሳ አርጀንቲና የሶስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ናት። በዘንድሮው ዓለም ዋንጫ በተመሳሳይ ስድስት ግቦችን ያስቆጠሩት ሃሪ ኬን እና ጁድ ቤሊንግሃም በዛሬው ጨዋታ የሚጠበቁ ተጫዋቾች ናቸው። የ39 ዓመቱ ሊዮኔል ሜሲ በጨዋታው ትኩረትን ያገኘ ተጫዋች ነው። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ስምንት ግቦችን በማስቆጠር ለኮከብ ግብ አግቢነት እየተፎካከረ ይገኛል። ሜሲ በአጠቃላይ በዓለም ዋንጫ 21 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ነው። የአማካይ ተጫዋቹ ሮድሪጎ ዲ ፖል ከአርጀንቲና በኩል በጨዋታው ልዩነት ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል። አርጀንቲና በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ በርካታ ግቦችን (17) ያስቆጠረች ሀገር ናት። እንግሊዝ ለሁለተኛ ጊዜ፣ አርጀንቲና ለሰባተኛ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ ለማለፍ ይፋለማሉ። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። አሸናፊው ሀገር ከስፔን ጋር በፍጻሜው ይገናኛል። ትናንት በተደረገው የመጀመሪያ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ስፔን ፈረንሳይን 2 ለ 0 በመርታት የፍጻሜው ተፋላሚ ሆናለች።
ስፔን ፈረንሳይን በመርታት ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ አለፈች
Jul 14, 2026 963
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ተጠባቂ የግማሽ ፍጻሜ መርሐ ግብር ስፔን ፈረንሳይን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በዳላስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማይክል ኦያርዛባል በ22ኛው ደቂቃ የመጀመሪያውን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት አስቆጥሯል። ፍጹም ቅጣት ምቱ የተገኘው የፈረንሳዩ ተከላካይ ሉካ ዲኝ በላሚን ያማል ላይ በሰራው ጥፋት ነው። የ29 ዓመቱ አጥቂ ኦያርዛባል በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት አምስት አድርሷል። ፔድሮ ፖሮ በ58ኛው ደቂቃ ሁለተኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ስፔን በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድሎችን በመፍጠር አንጻራዊ ብልጫ ነበራት። የፈረንሳይ የአጥቂ መስመር ክፍል በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያሳየውን አስፈሪነት በዛሬው ጨዋታ መድገም አልቻለም። በአጠቃላይ ፈረንሳይ በሚጠበቀው የብቃት ደረጃ ላይ አልነበረችም። የ25 ዓመቱ የፈረንሳይ ተከላካይ ዊሊያም ሳሊባ በ30ኛው ደቂቃ በጉዳት ምክንያት ተቀይሮ ወጥቷል። ውጤቱን ተከትሎ ስፔን ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ አልፋለች። ስፔን ከ19ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በኋላ ለሁለተኛ ጊዜ የፍጻሜውን ትኬት ቆርጣለች። የአንድ ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ስፔን በዘንድሮው ውድድር ምንም ሽንፈት ያላስተናገደች ሀገር ሆናለች። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫም የተቆጠረባት አንድ ግብ ብቻ ነው። ስፔን በፍጻሜው ከእንግሊዝ እና አርጀንቲና አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ለዋንጫው የተጠበቀችው ፈረንሳይ ለፍጻሜ መብቃት አልቻለችም። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ሽንፈቷን አስተናግዳለች። የሁለት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ፈረንሳይ ለአምስተኛ ጊዜ ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ የማለፍ ህልሟ ሳይሳካ ቀርቷል። ፈረንሳይ ከእንግሊዝ እና አርጀንቲና ተሸናፊ ጋር ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ትጫወታለች። በዓለም ዋንጫው ስምንት ጎሎችን ያስቆጠረው ኪሊያን እምባፔ ለሁለት ተከታታይ የዓለም ዋንጫ ፍጻሜ የማለፍ ህልሙ ሳይሳካ ቀርቷል። እምባፔ አሁንም ለከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱ መፎካከሩን ይቀጥላል። የ27 ዓመቱ አጥቂ 21ኛ የዓለም ዋንጫ በማድረግ ለፈረንሳይ በውድድሩ ላይ በርካታ ጨዋታዎችን ያደረገ ተጫዋች ሆኗል። በነዚህ ጨዋታዎች ላይ 20 ግቦችን አስቆጥሯል። ሁለተኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሐ ግብር ነገ በእንግሊዝ እና አርጀንቲና መካከል ይደረጋል።
ማን የፍጻሜውን ትኬት ይቆርጣል? ፈረንሳይ ወይስ ስፔን?
Jul 14, 2026 783
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 7/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ከሁለት ቀናት እረፍት በኋላ ዛሬ በግማሽ ፍጻሜ መርሐ ግብር ይመለሳል። ፈረንሳይ እና ስፔን ምሽት አራት ሰዓት ላይ በዳላስ ስታዲየም ለፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጉት ፍልሚያ የዓለም ትኩረት አርፎበታል። ፈረንሳይ በሩብ ፍጻሜው ሞሮኮን 2 ለ 0 በመርታት ለሶስት ተከታታይ ዓለም ዋንጫ ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። የሁለት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ፈረንሳይ ግማሽ ፍጻሜ ስትገባ የአሁኑ ለሰባተኛ ጊዜ ነው። ተጋጣሚዋ ስፔን ቤልጂየምን 2 ለ 1 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን የተቀላቀለች ሲሆን አራት ውስጥ ስትገባ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫ ከዚህ ቀደም አንድ ጊዜ ተገናኝተዋል። ጀርመን እ.አ.አ በ2006 ባዘጋጀችው 18ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ 16 ውስጥ ተገናኝተው ፈረንሳይ ስፔንን 3 ለ 1 በመርታት ለሩብ ፍጻሜው አልፋለች። ፍራንክ ሪቤሪ፣ ፓትሪክ ቪዬራ እና ቲዬሪ ሄነሪ በወቅቱ ለፈረንሳይ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ነበሩ። ዴቪድ ቪያ የስፔንን ብቸኛ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የአውሮፓ የእግር ኳስ ኃያላኑ ከ20 ዓመታት በኋላ በዓለም ግዙፉ የእግር ኳስ መድረክ ለፍጻሜ ለማለፍ ይፋለማሉ። በአጠቃላይ ሁለቱ ሀገራት በሁሉም የውድድር እና የወዳጅነት ጨዋታዎች 38 ጊዜ ተገናኝተው ስፔን 18 ጊዜ ስታሸንፍ ፈረንሳይ በ13ቱ ድል ቀንቷታል። በቀሪ ሰባት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ስፔን በ38ቱ ጨዋታዎች ላይ 71 ግቦችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ ፈረንሳይ 45 ጎሎችን ማስቆጠር ችላለች። ሁለቱ ሀገራት በሚያደርጓቸው ጨዋታዎች በአማካይ ከሶስት ጎሎች በላይ የሚቆጠር ሲሆን ይህም ቡድኖቹ ለማጥቃት እንቅስቃሴ ያላቸውን ፍላጎት የሚያሳይ ነው። በዓለም ዋንጫው ላይ ድንቅ ብቃቱን እያሳየ የሚገኘው የ27 ዓመቱ ኪሊያን ምባፔ በዛሬ ጨዋታ የሚጠበቅ ተጫዋች ነው። ምባፔ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ስምንት ጎሎችን በማስቆጠር ከአርጀንቲናው ሊዮኔል ሜሲ ጋር በጎል እኩል በመሆን ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል ብልጫ ወስዶ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ይገኛል። በአጠቃላይ በውድድሩ ላይ 20 ጎሎች ከመረብ ላይ በማሳረፍ በምንጊዜም ከፍተኛ አስቆጣሪነቱ ከሜሲ (21 ጎል) በአንድ አንሶ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ምባፔ በዓለም ዋንጫው የጥሎ ማለፍ ምዕራፍ 12 ጎሎችን በማስቆጠር በውድድሩ አዲስ ክብረ ወሰን አስመዝግቧል። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ አምስት ጎሎችን ከመረብ ላይ ያሳረፈው ኡስማን ዴምቤሌ እና አምስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን ያቀበለው ማይክል ኦሊሴም ልዩነት ፈጣሪ ተጫዋቾች ናቸው። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ አራት ጎሎችን ያስቆጠረው የ29 ዓመቱ አጥቂ ሚኬል ኦያርዛባል ከስፔን በኩል ትኩረትን የሳበ ተጫዋች ሆኗል። በዓለም ዋንጫው አንድ ግብ ያለው ላሚን ያማል እና የቡድኑ አምበል ሮድሪ የሚጠበቁ ተጫዋቾች ናቸው። ፈረንሳይ ለዓለም ዋንጫ ፍጻሜ ለአምስተኛ፣ ስፔን ደግሞ ለሁለተኛ ጊዜ ለማለፍ ይጫወታሉ። ጨዋታው ተመጣጣኝ እና አዝናኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። የዛሬው ጨዋታ አሸናፊ ከአርጀንቲና እና እንግሊዝ አሸናፊ ጋር በፍጻሜው ይገናኛል።
የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ክለብ ድል የጋራ ጥረት፣ ትጋትና አንድነት ውጤት ነው
Jul 13, 2026 610
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፡-የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ክለብ ያስመዘገበው ድል የጋራ ጥረት፣ ትጋት እና አንድነት ውጤት መሆኑ ተገለጸ፡፡ የ2018 ዓ.ም ሲቢኢ የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግና ከ20 ዓመት በታች አሸናፊ የሆነው የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ክለብ ዛሬ ሀዋሳ ከተማ ሲደርስ በከተማው ነዋሪዎችና በተለያዩ አካላት ደማቅ አቀባበል ተደርጎለታል።   በአቀባበል ሥነስርአቱ ላይ የተገኙት የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የትምህርት ቢሮ ሃላፊና የክልሉ ስፖርት ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ በየነ በራሳ እንደተናገሩት ክለቡ ያስመዘገበው ስኬት የጋራ ትብብርና የአንድነት ውጤት ነው። ክለቡ የህዝብ መሰረት ያለውና የሚደረግለትን ጠንካራ ድጋፍና ክትትል በአግባቡ በመጠቀም ስኬታማ መሆን እንደቻለ ያነሱት አቶ በየነ፣ አንድነትና ትጋት ካለ ለውጤት መብቃት እንደሚቻል ማሳያ ነው ብለዋል።   ክለቡ የተቀናጀ ድጋፍ በማግኘቱ ያስመዘገበውን ስኬት በአርአያነት ወስዶ በሌሎች የልማት መስኮችም ለመድገም መትጋት እንደሚገባ ገልጸው፣ ክለቡ ያስመዘገበው ውጤት ለክልሉ ህዝብም ኩራት መሆኑን ተናግረዋል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ክለቡ ሲበረታም ሆነ ሲደክም ከጎኑ በመሆን ላበረታቱት ደጋፊዎች ያላቸውን አክብሮት ገልጸዋል፡፡ በቀጣይ ዓመት ክለቡ በአፍሪካ ሻምፕዮንስ ሊግ በሚኖረው ውድድር የላቀ ውጤት እንዲያስመዘግብ የባለድርሻ አካላት ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም ጥሪ አቅርበዋል።   የክልሉ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ሃላፊና የክለቡ ቦርድ ሰብሳቢ አቶ ጃጎ አገኘሁ በበኩላቸው፣ ክለቡ ያስመዘገበው ድል የህዝቡ አንድነት፣ ትጋትና ጥረት ውጤት መሆኑን ተናግረዋል። የተጨዋቾች ትጋት፣ የክልሉ መንግስትና ህዝብ እንዲሁም የደጋፊዎች አስተዋጾ ክለቡን የድል ባለቤት እንዳደረገው ገልጸው፣ ባለድርሻ አካላት ላደረጉት የተቀናጀና ያልተቋረጠ ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።   ክለቡ ያስመዘገበው ድል በክልሉ በስፖርት ልማት ዘርፍ የሚከናወኑ ተግባራትን የሚያሳድግና መነቃቃትን የሚፈጥር መሆኑን ጠቅሰው ተተኪ ስፖርተኞች በበቂ ሁኔታ ለማፍራት ይሰራል ብለዋል፡፡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን ማልማትና ስፖርቱ ከመንግስት ድጋፍ ተላቆ የራሱ ሀብትና የገንዘብ ምንጭ እንዲኖረው የሁሉም ተሳትፎ መጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል።      
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫው ያልፍ ይሆን? 
Jul 12, 2026 749
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2018 (ኢዜአ)፦ ለ2026 የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የሚጫወተው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን፣ ወሳኙንና የመጨረሻውን የዙር መልስ ጨዋታ ዛሬ ከዛምቢያ ጋር ያካሂዳል። ጨዋታው ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይከናወናል። ሁለቱ ሀገራት ሰኔ 27 ቀን 2018 ዓ.ም በንዶላ ሌቪ ምዋናዋሳ ስታዲየም ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛምቢያ 2 ለ 1 አሸንፋለች። ፍሪዳ ንዳሼ እና ፒዳ ሙዙዋ የዛምቢያን ጎሎች አስቆጥረዋል። ምኅረት አየለ የኢትዮጵያን ብቸኛ ግብ ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ጨዋታው በዛምቢያ የተደረገ ቢሆንም፣ የኢትዮጵያ ታዳጊዎች ከሜዳቸው ውጪ ያስቆጠሯት ወሳኝ ጎል በአዲስ አበባው የመልስ ጨዋታ የማለፍ ዕድላቸው እንዲለመልም አድርጎታል። በአሰልጣኝ ራውዳ አሊ የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከመጀመሪያው ጨዋታ መልስ ዝግጅቱን በአዲስ አበባ ሲያደርግ ቆይቷል። ቡድኑ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ያከናወነ ሲሆን ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት እና የስነ ልቦና ዝግጁነት ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በልምምዱ ላይ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ምክትል ኘሬዝዳንት ዳኛቸው ንግሩ (ዶ/ር)፣ የፌዴሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ባሕሩ ጥላሁን፣ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል ወይዘሪት ብዙዓየሁ ጀምበሩ እና የካፍ ኤሊት ኢንስትራክተር አብርሃም መብራቱ በመገኘት ቡድኑን አበረታተዋል። ኢትዮጵያ በድምር ውጤት ካሸነፈች በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ ለፊፋ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ ማለፏን ታረጋግጣለች። በአንጻሩ ዛምቢያ ማሸነፍ ወይም አቻ መውጣት ከቻለች ለሦስተኛ ተከታታይ ጊዜ በዓለም ዋንጫው መሳተፏን ታረጋግጣለች። በርካታ ደጋፊ በስታዲየሙ በመገኘት ለታዳጊ ብሔራዊ ቡድኑ ድጋፍ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል። በሞሮኮ አስተናጋጅነት በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም ለሚካሄደው 10ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ዓለም ዋንጫ 24 አገራት ይሳተፋሉ። የአፍሪካ አህጉር በውድድሩ ላይ በአምስት አገራት የምትወከል ሲሆን፣ ከአስተናጋጇ ሞሮኮ ውጪ አህጉሪቱን ወክለው ወደ ዓለም ዋንጫው የሚጓዙት ቀሪዎቹ አራት አገራት በመጨረሻው ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች ተለይተው ይታወቃሉ።
የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገፅታ ከመቀየር ባለፈ ለስፖርቱ ዘርፍ ትልቅ መነቃቃት ፈጥሯል - ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን
Jul 12, 2026 735
አሶሳ፤ ሐምሌ 5/2018 (ኢዜአ)፡- የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለስፖርቱ ዘርፍ ትልቅ መነቃቃት መፍጠሩን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ገለጹ። የአሶሳ ከተማ የመጀመሪያው የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ "ለኮሪደር ልማትና ለከተማ ውበት እሮጣለሁ" በሚል መሪ ሃሳብ ዛሬ ማለዳ ተካሂዷል።   በመርሃግብሩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ የአሶሳ ከተማ ነዋሪዎች ተገኝተዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን በወቅቱ እንደተናገሩት፤ የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገፅታ በመቀየር የተለያዩ አገልግሎቶች ለነዋሪዎች ተደራሽ እንዲሆኑ አድርጓል። የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማትም ከተማዋን በማዘመን ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትሆን ከማድረግ ባለፈ በርካታ የስፖርት ማዘውተሪያ በታዎችን በመገንባት ለዘርፉ ትልቅ መነቃቃት መፍጠሩን ገልጸዋል።   በዚህም የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያሳተፈ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ በተለዬ ሁኔታ እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመው፥ የዛሬው የጎዳና ላይ ሩጫም የኮሪደር ልማቱ ለስፖርቱ የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ ይበልጥ የሚያመላክት ነው ብለዋል የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ኢብራሂም መንሱር በበኩላቸው፤ መንግስት ለስፖርቱ ዘርፍ በሰጠው ትኩረት በርካታ የስፖርት መሠረተ ልማቶች እየተገነቡ መሆኑን አንስተዋል። እንደዚህ ዓይነት የጎዳና ላይ ሩጫ የአትሌቲክስ ስፖርትን ከማነቃቃት ባለፈ በህዝቦች መካከል ያለውን ማህበራዊ ትስስር ለማጠናከር እንደሚያግዝም ጠቁመዋል።   በውድድሩ አሸናፊ ለሆኑ ሯጮችም ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።  
የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ያዘጋጀው የ5 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር እየተካሄደ ነው
Jul 12, 2026 1403
አዲስ አበባ ፤ሐምሌ 5 /2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ያዘጋጀው የ5 ኪሎ ሜትር ታላቁ የሩጫ ውድድር በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ እየተካሄደ ይገኛል። "ኢትዮጵያ እየመከረች ነው" በሚል መሪ ሃሳብ በመስቀል አደባባይ እየተካሄደ ባለው በዚህ መርሃ ግብር ላይ ሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶችን ጨምሮ በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች በመሳተፍ ላይ ናቸው። በአሁኑ ወቅትም የውድድሩ ተሳታፊዎች ከሩጫው አስቀድሞ በተዘጋጀው የጋራ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ላይ በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። የኢትዮጵያ ዋናው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ከመጪው ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባ የሚካሄድ ሲሆን፤ በዋናው ጉባኤ ላይ የሚሳተፉ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር የሕዝብ ወኪሎችም ወደ አዲስ አበባ በመግባት ላይ ናቸው። በዚህ ዋና የምክክር ጉባኤ ላይ፡ • የሀገር ግንባታ፣ • የመንግሥት አደረጃጀትና ቅርጽ፣ • የፖለቲካ ሥርዓት፣ ውክልና እና የምርጫ ሥርዓት፣ • የፌዴራል ከተሞች (አዲስ አበባና ድሬዳዋ) ጉዳይ፣ • የሃይማኖት ጉዳዮች፣ • የተቋማት ግንባታ፣ የሕግ የበላይነትና ሰብዓዊ መብቶች፣ • ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች (የአርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች ጉዳይን ጨምሮ)፣ • እንዲሁም ሙስና፣ መልካም አስተዳደርና የሰላም ግንባታን ያካተቱ ስምንት ዐበይት አጀንዳዎች ላይ የሕዝብ ወኪሎች የሚመክሩባቸው ይሆናል። በመስቀል አደባባይ በተሰናዳው በዚህ የአምስት ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር መርሃ ግብር ላይ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አቶ አዝመራው አንደሞ፣ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ እንዲሁም የኮሚሽኑ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ኮሚሽነሮች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም