ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የኢትዮጵያ የዓለም አትሌቲክስ የጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና ዝግጅት
Sep 14, 2026 117
አዲስ አበባ፤መስከረም 4 /2019 (ኢዜአ):- ሁለተኛው የዓለም አትሌቲክስ የጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና መስከረም 9 እና 10 ቀን 2019 ዓ.ም በዴንማርክ ኮፐንሃገን ይካሄዳል። በሻምፒዮናው ላይ ከ86 ሀገራት የተወጣጡ 496 አትሌቶች ይሳተፋሉ። በተጨማሪም የዓለም አትሌቲክስ የስደተኞች አትሌቲክስ ቡድንም በዚህ ውድድር ላይ ተካፋይ ነው። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ላይ ከሚሳተፉ ሀገራት መካከል አንዷ ነች። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልዑካን ቡድን በአዲስ አበባ ዝግጅቱን እያደረገ ይገኛል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኮማንደር አትሌት ስለሺ ስህን፣ የቡድኑ መሪ ኢንስትራክተር አድማሱ ሳጂ እና የቴክኒክ ቡድኑ መሪ አቶ አሰፋ በቀለ በስታዲየሙ በመገኘት አትሌቶቹን አበረታተዋል። የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት ኮማንደር አትሌት ስለሺ ስህን ለሻምፒዮናው የሚያስፈልገውን ዝግጅት ፌዴሬሽኑ ከወዲሁ እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። አትሌቶቹ በትጋት እንዲዘጋጁ ያበረታቱ ሲሆን በኮፐንሀገን በሚያደርጉት ተሳትፎም መልካም ውጤት እንዲያስመዘግቡ ተመኝተዋል። አትሌቶቹም ከኮፐንሀገን የአየር ንብረትና የውድድር ሁኔታ ጋር በተሻለ ሁኔታ ለመላመድ በእንጦጦ፣ በጣፎ፣ በ4 ሺህ አካባቢ፣ ቃሊቲ፣ ሰበታ እና ሰንዳፋን ጨምሮ በተለያዩ ስፍራዎች የልምምድ ዝግጅታቸውን እያከናወኑ ይገኛሉ። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ላይ በወንዶችና በሴቶች ግማሽ ማራቶን፣ በወንዶችና በሴቶች አምስት ኪሎ ሜትር እንዲሁም በሴቶች አንድ ማይል ውድድሮች ተሳትፎ ታደርጋለች። የዓለም አትሌቲክስ የጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና የቀድሞውን የዓለም አትሌቲክስ የግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና የተካ ውድድር ነው። የግማሽ ማራቶን ሻምፒዮናው ከእ.አ.አ 1992 እስከ 2020 ሲካሄድ ቆይቷል። እ.አ.አ በ2023 ስያሜውን ቀይሮ የዓለም አትሌቲክስ የጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና የተባለ ሲሆን የመጀመሪያው ውድድር በዛው ዓመት በላቲቪያ ሪጋ ተካሄዷል። የአሁኑ ሻምፒዮና ከዚህ ቀደም ከነበረው የግማሽ ማራቶን በተጨማሪ የአምስት ኪሎ ሜትር እና የአንድ ማይል ውድድሮች ተካተውበታል።
በሳምንቱ መጨረሻ በተደረጉ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድሮች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ድል ቀንቷቸዋል
Sep 14, 2026 104
አዲስ አበባ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት በተከናወኑ የጎዳና ላይ ውድድሮች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች አሸንፈዋል። በታይላንድ በተካሄደው የባንግሳኤን 10 ኪሜ ውድድር በወንዶች አትሌት ሰውመሆን አንተነህ 28:28 በሆነ ጊዜ አሸናፊ ሲሆን፣ አትሌት ገላና ተሾመ 28:40 በማስመዝገብ ሁለተኛ ወጥቷል። አትሌት ጫለቺሳ ገለታ ደግሞ 29:31 በማስመዝገብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በሴቶች ውድድር አትሌት ውብርስት አስቻለ 32:14 በሆነ ጊዜ ሁለተኛ ስትሆን፣አትሌት ቢቂሌ አመሱ 32:31 በማስመዝገብ ሦስተኛ ወጥታለች። አትሌት በቀሽ ኦላኒ 33:14 አራተኛ፣ አትሌት ዱሌ ምትኩ 33:53 ሰባተኛ እና አትሌት ስለእናት ቢተው 33:56 ስምንተኛ ደረጃን ይዘዋል። በቻይና ሃርቢን ማራቶን በወንዶች አትሌት ያሚ ዳዲ 2:12:41 በሆነ ጊዜ የወንዶችን ውድድር ሲያሸንፍ፣ በሴቶች አትሌት ቡርቱካን ይፍሩ 2:30:19 በሆነ ጊዜ አንደኛ ወጥታለች። አትሌት ገብሬላ ዮሐንስ 2:30:26 ሁለተኛ፣አትሌት ንፁህ ነገሰ 2:34:01 ሦስተኛ ደረጃን ይዘዋል። በጀርመን ሙንስተር ማራቶን አትሌት አገሬ በላቸው 2:28:43 በሆነ ጊዜ የሴቶችን ውድድርን አሸንፋለች አትሌት አዛለች ማረሻ ደግሞ 2:31:09 በማስመዝገብ ሦስተኛ ወጥታለች። በስሪላንካ ኮሎምቦ ማራቶን አትሌት አይናለም ካሳሁን 2:54:09 በሆነ ጊዜ የሴቶችን ውድድር አሸንፋለች። አትሌት ጌጤ ጉታ 2:54:48 ሁለተኛ፣አትሌት ገንዘብ ሹሚ 2:55:20 ሦስተኛ በመሆን የኢትዮጵያን የበላይነት አረጋግጠዋል። በወንዶች አትሌት ነጋሲ ቱጂ ኮርሜ 2:21:50 በሆነ ጊዜ ሦስተኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። በእንግሊዝ ግሬት ኖርዝ ግማሽ ማራቶን አትሌት መልክናት ውዱ 1:09:37 በሆነ ጊዜ ሦስተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። በፖርቹጋል የፖርቶ ግማሽ ማራቶን አትሌት ሕይወት መሐሪ 1:12:07 በሆነ ጊዜ ሦስተኛ ስትወጣ፣ በወንዶች አትሌት ንጉስ መኮንን 1:03:52 በማስመዝገብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። በታይላንድ ክራቢ ግማሽ ማራቶን ደግሞ አትሌት ፀጋይ ኪሮስ 1:08:58 በሆነ ጊዜ ሁለተኛ፣አትሌት ገመቹ ዲዳ 1:09:15 ሦስተኛ ደረጃን ይዘዋል። በሴቶች አትሌት ማርታ ብርሃን 1:23:01 በማስመዝገብ ሦስተኛ ወጥታለች። በስሎቫኪያ በተካሄደው የብሩዝ የምሽት 10 ኪሜ ውድድር አትሌት መልኬነህ አዜዜ 27:40 በሆነ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሲሆን፣አትሌት ሽመልስ ንጉሴ 27:50 በማስመዝገብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል።
ሊድስ ዩናይትድ ከኒውካስትል ዩናይትድ: የአራተኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታ
Sep 14, 2026 101
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ አራተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ሊድስ ዩናይትድ ከኒውካስትል ዩናይትድ በኤላንድ ሮድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባለሜዳው ሊድስ ዩናይትድ ከሶስት ጨዋታዎች አምስት ነጥብ በማግኘት 11ኛ ደረጃን ይዟል። ኒውካስትል ዩናይትድ በተመሳሳይ አምስት ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች ከዚህ ቀደም በሊጉ 30 ጊዜ ተገናኝተው ኒውካስትል ዩናይትድ በ13ቱ ድል ሲቀናው ሊድስ ዩናይትድ ሰባት ጊዜ አሸንፏል። በቀሪ 10 ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርተዋል። ኒውካስትል ዩናይትድ በ30ዎቹ ጨዋታዎች ላይ 45 ግቦችን ሲያስቆጥር ሊድስ ዩናይትድ 42 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቡድኖቹ ባለፉት አምስት የሊግ ግንኙነታቸው ኒውካስትል ዩናይትድ በሁለቱ ሲያሸንፍ በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ሊድስ ዩናይትድ ኒውካስትልን ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ ያሸነፈው እ.አ.አ በ2021 ሲሆን በወቅቱ የ2 ለ 1 ድል ተቀዳጅቷል። ባለሜዳው ሊድስ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ኒውካስትል ዩናይትድ በሶስተኛ ሳምንት ከቦርንማውዝ ጋር ሁለት አቻ ተለያይቷል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ41 ዓመቱን ማይክል ሳሊስበሪ ጨዋታውን በመሐል ዳኝነት እንዲመሩ ተመድበዋል።
በተጠባቂው የደርቢ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Sep 13, 2026 396
አዲስ አበባ፤ መስከረም 3/2019 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ማንችስተር ሲቲ ማንችስተር ዩናይትድን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኦልትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሊንግ ሃላንድ በ60ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ሃላንድ በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ አራት በማድረስ የከፍተኛ ጎል አስቆጣሪነቱን መምራት ጀምሯል። የማንችስተር ሲቲው ፊል ፎደን በ23ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ባለሜዳው ማንችስተር ዩናይትድ ያገኘውን የቁጥር ብልጫ መጠቀም አልቻለም። በ10 ተጫዋች አብዛኛውን የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ለመጫወት የተገደደው ማንችስተር ሲቲ ድል ቀንቶታል። በ199ኛው የማንችስተር ደርቢ ድል የቀናው ሲቲ በ12 ነጥብ ተመሳሳይ ነጥብ ባለው አርሰናል በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ማንችስተር ዩናይትድ በአራት ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቀን ላይ በተደረገ ጨዋታ ብራይተን ኮቨንተሪ ሲቲን 5 ለ 0 ረትቷል።
ሲዳማ ቡና ቻዱ ክለብ ኤግሎስን 3ለ0 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር አለፈ
Sep 13, 2026 313
አዲስ አበባ፤መስከረም 3 /2019 (ኢዜአ):-ኢትዮጵያን በአፍሪካ ሻምፒየንስ ሊግ እየወከለ የሚገኘው ሲዳማ ቡና ቻዱ ክለብ ኤግሎስን 3ለ0 በማሸነፍ ወደ ሁለተኛው ዙር ማጣሪያ ማለፉን አረጋግጧል። የሲዳማ ቡናን የማሸነፊያ ግቦች አቤል ያለው ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር እና ደስታ ደሙ ቀሪዋን ማስቆጠር ችለዋል። በሁለተኛው ዙር ሲዳማ ቡና ከሱዳኑ ክለብ አል ሂላል ጋር የሚጫወት ይሆናል።
ሲዳማ ቡና የካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ የመልስ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል
Sep 13, 2026 145
አዲስ አበባ፤ መስከረም 3 /2019 (ኢዜአ):- በካፍ ሻምፒዮንስ የመጀመሪያ ዙር ቅድመ ማጣሪያ ሲዳማ ቡና ከቻዱ ኤግሎንስ ጋር ዛሬ ሁለተኛ ጨዋታውን ያከናውናል። ጨዋታው ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ሁለቱ ክለቦች ነሐሴ 30 ቀን 2018 ዓ.ም በቻድ ንጃሚና ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። በጨዋታው ላይ ሲዳማ ቡና ጠንካራ የመከላከል እንስቃሴ ያሳየ ቢሆንም ግልጽ የግብ እድሎች መፍጠር ላይ ክፍተቶች ታይተውበታል። በአንጻሩ ተጋጣሚው አይግሎንስ በቆሙ ኳሶች እና በመልሶ ማጥቃት እንቅሰቃሴ ግብ ለማስቆጠር ሙከራዎችን አድርጓል። ሲዳማ ቡና ወደ ቀጣዩ ዙር ለማለፍ የማጥቃት አቅሙን ማሻሻል ይጠበቅበታል። ከተጋጣሚው በኩል ከቆሙ ኳሶችና ከፈጣን ሽግግሮች የሚመጡ ኳሶችን መግታት ይጠበቅበታል። በያሬድ ገመቹ የሚመራው ሲዳማ ቡና በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ውድድር ላይ ለመሳተፍ የበቃው የ2018 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮንመሆኑን ተከትሎ ነው። በ1999 ዓ.ም የተቋቋመው ሲዳማ ቡና በአህጉራዊ መድረክ ሲሳተፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ሲዳማ ቡና በዛሬው ጨዋታ ማሸነፍ ወደ ሁለተኛው ዙር ያሳልፈዋል። ሲዳማ ቡና በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ በሁለተኛው ዙር ማጣሪያ ከሱዳኑ አል ሂላል እና ከብሩንዲው አይግል ኑዋር አሸናፊ ጋር ይጫወታል።
199ኛው የማንችስተር ደርቢ
Sep 13, 2026 147
አዲስ አበባ፤ መስከረም 3/2019 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ አራተኛ ሳምንት ማንችስተር ዩናይትድ ከማንችስተር ሲቲ ዛሬ የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ የተመልካቾችን ቀልብ ስቧል። ጨዋታው ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ላይ በኦልድትራፎርድ ስታዲየም ይካሄዳል። ማንችስተር ዩናይትድ በአራት ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ በዘጠኝ ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በሁሉም ውድድሮች ሲገናኙ የአሁኑ ለ199ኛ ጊዜ ነው። ቡድኖቹ ከዚህ በፊት ባደረጓቸው 198 ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ 81 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ 63 ጊዜ ሲያሸንፍ 54 ጊዜ ነጥብ ተጋርተዋል። በፕሪሚየር ሊጉ 58 ጊዜ ተገናኝተው ማንችስተር ዩናይትድ 27 ጊዜ ሲያሸንፍ ሲቲ በ21ዱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ 10 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሁለቱም ክለቦች በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ አሸንፈዋል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። ማንችስተር ዩናይትድ እና ማንችስተር ሲቲ የአንድ ከተማ ባላንጣ ቡድኖች ናቸው። ክለቦቹ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ1881 ነበር። በዚህ ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ 3 ለ 0 አሸንፏል። ቡድኖቹ ከመጀመሪያ ጨዋታቸው አንስቶ ለ145 ዓመታት የቆየ ፉክክር በእንግሊዝ እና በአውሮፓ መድረክ አድርገዋል። ማንችስተር ዩናይትድ የሊጉን ዋንጫ 20 ጊዜ በማንሳት የበላይነቱን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ 10 ጊዜ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ሆኗል። ሁለቱ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ ለመጨረሻ ጊዜ የተጋናኙት በጥር ወር 2018 ዓ.ም ሲሆን በወቅቱ ማንችስተር ዩናይትድ 2 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ማንችስተር ዩናይትድ በሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከኤቨርተን ጋር ሁለት አቻ ተለያይቷል። በጨዋታው ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። የከተማ ተቀናቃኙ ማንችስተር ሲቲ በሶስቱም የሊጉ ጨዋታዎች አሸንፏል። ዛሬ ድል ቀናው የሊጉን መሪነት ከአርሰናል በድጋሚ የመረከብ እድል አለው። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ41 ዓመቱ ማይክል ኦሊቨር ተጠባቂውን የደርቢ ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በዕለቱ ሌላኛው መርሐ ግብር ኮቨንተሪ ሲቲ ከብራይተን በኮቨንተሪ ቢውልዲንግ ሶሳይቲ አሬና ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
አርሰናል የሊጉን መሪነት ከማንችስተር ሲቲ ተረከበ
Sep 12, 2026 271
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ):- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት መርሐ ግብር አርሰናል ሰንደርላንድን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በስታዲየም ኦፍ ላይት በተደረገው ጨዋታ አዲስ ፈራሚ ብሩኖ ጉማራይሽ በ58ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ የመጀመሪያውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በ75 ሚሊዮን ፓውንድ ከኒውካስትል ዩናይትድ የፈረመው ጉማራይሽ የመጀመሪያ ጎሉን አስቆጥሯል። ግቧ የተቆጠረችው የሰንደርላንዱ ኤንዞ ላፌ በ56ኛው ደቂቃ ፍጹም ቅጣት ምት ከሳተበት አጋጣሚ በኋላ ነው። ፍጹም ቅጣት ምቱን የአርሰናሉ ግብ ጠባቂ ዴቪድ ራያ በግሩም ሁኔታ አድኖታል። ቡካዮ ሳካ በ97ኛው ደቂቃ ሁለተኛውን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ አሳርፏል። በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ጎሉን አስቆጥሯል። የሰንደርላንዱ ሬናልዶ በሁለት ቢጫ በ96ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ወጥቷል። ጨዋታው ተመጣጣኝ እና አዝናኝ ፉክክር ተደርጎበታል። አራተኛ የሊግ ድሉን ያስመዘገበው የወቅቱ ሻምፒዮን አርሰናል በ12 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከማንችስተር ሲቲ ተረክቧል። በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሰንደርላንድ በአራት ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሰንደርላንድ ከእ.አ.አ 2009 በኋላ አርሰናልን በሊጉ አሸንፎ አያውቅም።
ቶተንሃም ሆትስፐርስ ባለማሸነፍ ጉዞው ቀጥሏል
Sep 12, 2026 265
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ):-በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ኤቨርተን ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው ማምሻውን በቶተንሃም ሆትስፐርስ ስታዲየም ተከናውኗል። ባለሜዳው ቶተንሃም የኳስ ቁጥጥር ብልጫን ቢወስድም ግብ ማስቆጠር ተስኖታል። ተጋጣሚው ኤቨርተን የተሻሉ የግብ እድሎችን መፍጠር ችሏል። በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት 334 ሚሊዮን ፓውንድ ያወጣው ቶተንሃም በአራት የሊግ ጨዋታዎች ግብ ማስቆጠር አልቻለም። በሁለት ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኤቨርተን በስድስት ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ሰንደርላንድ ከአርሰናል በስታዲየም ኦፍ ላይት የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ቼልሲ እና ሊቨርፑል ነጥብ ጣሉ
Sep 12, 2026 235
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ):- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች በመካሄድ ላይ ናቸው። በስታምፎርድ ብሪጅ በተካሄደው ጨዋታ ቼልሲ ከሁል ሲቲ ያደረገው ጨዋታ ሁለት አቻ ተጠናቋል። ሞርጋን ሮጀርስ እና ጆአኦ ፔድሮ ለቼልሲ ግቦቹን አስቆጥረዋል። መሐመድ ቤሉሚ ለሁል ሲቲ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቼልሲ በሰባት አራተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም። አዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ በስምንት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ክለቡ እስከ አሁን ምንም ሽንፈት አላስተናገደም። በሌላኛው መርሐ ግብር ሊቨርፑል ከፉልሃም ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ኖቲንግሃም ፎረስት አስቶንቪላን 2 ለ 1፣ ኤፕስዊች ታውን ክሪስታል ፓላስን 3 ለ 2 አሸንፈዋል። ቦርንማውዝ ከብሬንትፎርድ ሁለት አቻ ተለያይተዋል።
በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ወደ ቀጣዩ ዙር አለፈ
Sep 12, 2026 186
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ):- በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ የመጀመሪያ ቅድመ ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የሱዳኑን ሂላል አል-ሳሂልን 2 ለ 1 አሸንፏል። በድሬዳዋ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ካርሎስ ዳምጠው በ50ኛው እና በ56ኛው ደቂቃ ግቦቹን አስቆጥሯል። ኢንሳ ሰኢድ ለሂላል አል-ሳሂል ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሁለቱ ቡድኖች በድምር ውጤት ሶስት አቻ መሆናቸውን ተከትሎ ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቷል። በዚህም ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በመለያ ምት 4 ለ 1 በማሸነፍ ወደ ሁለተኛ ዙር ማጣሪያ አልፏል። ወልዋሎ በሁለተኛው ዙር ከዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም እና ከሊቢያው አል አህሊ ትሪፖሊ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። አል አህሊ ትሪፖሊ በመጀመሪያው ጨዋታ 3 ለ 0 ያሸነፈ ሲሆን የመልሱ ጨዋታ ዛሬ ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ ይደረጋል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በአህጉራዊ መድረክ ሲሳተፍ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። የውድድሩ ተሳትፎውን ያረጋገጠው የኢትዮጵያ ዋንጫ ማሸነፉን ተከትሎ ነው።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሂላል አል-ሳሂል፤ የካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ የማጣሪያ መልስ ጨዋታ
Sep 12, 2026 129
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ):- በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ የመጀመሪያ ቅድመ ማጣሪያ ዙር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የመልስ ጨዋታውን ዛሬ ከሱዳኑ ሂላል አል-ሳሂል ጋር ያከናውናል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 10 ሰዓት በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ሁለቱ ክለቦች ነሐሴ 29 ቀን 2018 ዓ.ም በሩዋንዳ በሚገኘው ኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የ2 ለ 1 ሽንፈት አስተናግዷል። ዋሊድ አል-ሻላ እና ፋሪስ ሞሂ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ካርሎስ ዳምጠው ለወልዋሎ ጎሏን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሜዳው ውጪ ወሳኝ ጎል አስቆጥሮ ተመልሷል። በአህጉራዊ መድረክ ለመጀመሪያ ጊዜ እየተሳተፈ የሚገኘው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በመጀመሪያ ጨዋታ በተለይም በመጀመሪያው አጋማሽ ጥሩ የማጥቃት እንቅሰቃሴ አድርጓል። በሁለተኛው አጋማሽ ቡድኑ በተጋጣሚው ብልጫ የተወሰደበት ሲሆን ፋሪስ ሞሂ የማሸነፊያውን ጎል ያስቆጠረው በዚሁ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ነው። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በዛሬው ጨዋታ ከአንድና ከዚያ በላይ የግብ ልዩነት ማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር ያሸጋግረዋል። ቡድኑ በጨዋታው የግድ ግብ የሚያስፈልገው በመሆኑ የጎል እድሎችን በሚገባ መጠቀም ይኖርበታል። ተጋጣሚው ሊከተለው የሚችለውን የመልሶ ማጥቃት እና የክንፍ መስመር እንቅስቃሴ መግታት ይጠበቅበታል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ በሁለተኛ ዙር ከዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም እና ከሊቢያው አል አህሊ ትሪፖሊ አሸናፊ ጋር የሚጫወት ይሆናል።
የዕለቱ ተጠባቂ ጨዋታዎች: አርሰናል ከሰንደርላንድ፣ ቼልሲ ከሁል ሲቲ እና ሊቨርፑል ከፉልሃም
Sep 12, 2026 153
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ አራተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጀመራል። በዕለቱ ሰባት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ሰንደርላንድ ከአርሰናል በስታዲየም ኦፍ ላይት ይጫወታሉ። ባለሜዳው ሰንደርላንድ ከሶስት ጨዋታዎች አራት ነጥብ በመሰብሰብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። የወቅቱ የሊጉ ሻምፒዮን አርሰናል ሶስቱንም ጨዋታዎች በማሸነፍ በዘጠኝ ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ሁለቱ ክለቦች በሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ35ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 34 ጨዋታዎች አርሰናል 20 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ሰንደርላንድ ያሸነፈው በሶስት አጋጣሚዎች ነው። በቀሪ 11 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ሰንደርላንድ አርሰናልን ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ ያሸነፈው እ.አ.አ በ2009 ነው። አርሰናል ዛሬ ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ከማንችስተር ሲቲ ይረከባል። ሁለቱ ቡድኖች ባለፈው የውድድር ዓመት በስታዲየም ኦፍ ላይት ባደረጉት የሊግ ጨዋታ ሁለት አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ቼልሲ በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም ሁል ሲቲን ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ያስተናግዳል። ቼልሲ በስድስት ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር በአርሰናል የ2 ለ 1 ሽንፈት አስተናግዷል። አዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ ከሶስት ጨዋታዎች ሰባት ነጥብ በመሰብሰብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለሜዳው ቼልሲ ከሽንፈቱ በማገገም ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታል። በአንጻሩ በሊጉ ጠንካራ ጅማሮ ያደረገው ሁል ሲቲ ለተጋጣሚው ፈተና ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል። ሊቨርፑል ከፉልሃም ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ከሶስት የሊግ ጨዋታዎች አምስት ነጥብ ያገኘው ሊቨርፑል በአምስት ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በሶስተኛ ሳምንት ኤፕስዊች ታውንን 2 ለ 0 በመርታት የመጀመሪያ ድሉን አሳክቷል። በአንጻሩ በሶስቱም የሊጉ ጨዋታዎች ሽንፈት ያስተናገደው ፉልሃም ያለ ምንም ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ሊቨርፑል ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ፉልሃም የመጀመሪያ ሶስት ነጥቡን ለማግኘት የሚያደርጉት ነው። አስቶንቪላ ከኖቲንግሃም ፎረስት፣ ክሪስታል ፓላስ ከኤፕስዊች ታውንና ቦርንማውዝ ከብሬንትፎርድ በተመሳሳይ 11 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከኤቨርተን በቶተንሃም ሆትስፐርስ ስታዲየም ይጫወታሉ።
ማንችስተር ዩናይትድ እና ባየር ሙኒክ ድል ቀንቷቸዋል
Sep 11, 2026 186
አዲስ አበባ፤ መስከረም 1/2019 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ትናንት ማምሻውን አራት ጨዋታዎች ተካሄደዋል። በኦልትራፎርድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ ሳባህን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማትያስ ኩንያ፣ ብሩኖ ፈርናንዴዝ፣ ቤንጃሚን ሼሽኮ እና ሊሳንድሮ ማርቲኔዝ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ባለሜዳው ማንችስተር ዩናይትድ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። የአዘርባጃኑ ሳባህ በውድድሩ ላይ ሲሳተፍ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ባየር ሙኒክ ቦዶ ግሊምትን 5 ለ 0 ረትቷል። ማይክል ኦሊሴ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ጀማል ሙሲያላ፣ ሃሪ ኬን እና አልፎንሶ ዴቪስ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የጀርመኑ ክለብ በመጀመሪያ አጋማሽ ከተጋጣሚው ፈተና ቢገጥመውም በሁለተኛው ክፍለ ጊዜ ግቦቹን በማስቆጠር ማሸነፍ ችሏል። በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመጀመሪያ ጊዜ እየተሳተፈ የሚገኘው የጣልያኑ ክለብ ኮሞ አርቢ ላፕዚግን 4 ለ 1 አሸንፏል። ሌንስ ስላቪያ ፕራግን 3 ለ 2 ማሸነፍ ችሏል። ትናንት አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ፊነርባቼ ከሮማ ፣ ፒኤስቪ ከሻካታር ዶኔስክ በተመሳሳይ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የመጀመሪያ ዙር መርሐ ግብር ተጠናቋል። ሁለተኛ ዙር የሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታዎች በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም መግቢያ ይካሄዳሉ።
ፊነርባቼ ከሮማ፣ ፒኤስቪ ከሻካታር ዶኔስክ ያደረጓቸው ጨዋታዎች በአቻ ውጤት ተጠናቀቁ
Sep 10, 2026 289
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሊግ ምዕራፍ ጨዋታዎች መካሄዳቸውን ቀጥለዋል። ማምሻውን በሱክሩ ሳራኮግሉ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፊነርባቼ እና ሮማ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። አርቺ ብራውን ለፊነርባቼ፣ ብራያን ክሪስታንቴ ለሮማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በፊሊፕስ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው መርሐ ግብር ፒኤስቪ አይንድሆቨን ከሻካታር ዶኔስክ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሰርጂኖ ዴስት ለፒኤስቪ ግቧን ሲያስቆጥር ግሊከር ሜንዶዛ የሻካታርን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል።
ባየር ሙኒክ ከቦዶ ግሊምት እና ማንችስተር ዩናይትድ ከሳባህ: የዕለቱ ተጠባቂ መርሐ ግብሮች
Sep 10, 2026 195
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ):- የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሊግ ምዕራፍ የመጀመሪያ ዙር መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። ባየር ሙኒክ የኖርዌውን ቦዲ ግሊምት ምሽት አራት ሰዓት ላይ በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም ያስተናግዳል። የስድስት ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ባለቤቱ ባየርን ባለፈው የውድድር ዓመት እስከ ግማሽ ፍጻሜ ደርሷል። በሻምፒዮንስ ሊጉ የሊግ ምዕራፍ ለሁለተኛ ጊዜ የሚሳተፈው ቦዶ ግሊምት ባለፈው የውድድር ዓመት 16 ውስጥ ገብቷል። ቦዶ ግሊምት በጉዞው ማንችስተር ሲቲ፣ አትሌቲኮ ማድሪድ እና ኢንተር ሚላን ያሸነፈበት መንገድ በእግር ኳስ አፍቃሪያን አድናቆት አስችሮታል። በዛሬውም ጨዋታም ሙኒክን ይፈትነዋል ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሐ ግብር ማንችስተር ዩናይትድ ከሳባህ ምሽት አራት ሰዓት ላይ በኦልድትራፎርድ ስታዲየም ይጫወታሉ። የሶስት ጊዜ የሻምፒዮንስ ሊግ ሻምፒዮኑ ማነችስተር ዩናይትድ ከእ.አ.አ 2023/24 የውድድር ዓመት በኋላ ወደ አውሮፓ መድረክ ተመልሷል። እ.አ.አ በ2017 የተመሰረተው የአዘርባጃኑ ሳባህ ለመጀመሪያ ጊዜ በሻምፒዮንስ ሊጉ ተሳትፎ ያደርጋል። በሌሎች መርሐ ግብሮች በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚሳተፈው የጣልያኑ ኮሞ ከአርቢ ላይፕዚግ እና ስላቪያ ፕራግ ከሌንስ በተመሳሳይ ምሽት አራት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ፊነርባቼ ከሮማ እና ፒኤስቪ አይንድሆቨን ከሻካታር ዶኔስክ በተመሳሳይ ምሽት 1 ሰዓት ከ45 ላይ ይጫወታሉ።
ባርሴሎና ሻምፒዮንስ ሊጉን በድል ጀምሯል
Sep 10, 2026 274
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ባርሴሎና ፌይኖርድን 5 ለ 1 ረትቷል። ማምሻውን በካምፕ ኑ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ራፊንሃ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ላሚን ያማል፣ ካሪም አዲዬሚ እና ጋብርኤል ጄሱስ ቀሪዎቹን ጎሎች ለባርሳ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሴም ስቴጅን ለፌይኖርድ ብቸኛውን ግብ አስቆጥሯል። በጨዋታው ባርሴሎና ፍጹም የበላይነት ወስዷል። የባርሴሎናው አምበል ራፊንሃ በዘንድሮው የውድድር ዓመት ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ስምንት አድርሷል። የካታላኑ ክለብ ዘንድሮ ያደረጋቸውን አምስት ጨዋታዎች ያሸነፈ ሲሆን 22 ጎሎችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ቡድኑ በጠንካራ ጅማሮው ቀጥሏል። በሌላኛው መርሐ ግብር ስቱትጋርት ቫይኪንግን 3 ለ 1 አሸንፏል። በኤምኤችፒ አሬና በተደረገው ጨዋቻ ኤርሜዲን ዴሚሮቪች ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። የ28 ዓመቱ ቦስኒያዊ አጥቂ በዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ ሀትሪክ የሰራ የመጀመሪያ ተጫዋች ሆኗል። ዝላትኮ ትሪፒች ለኖርዌው ክለብ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል።
ፒኤስጂ፣ አርሰናል እና ሊቨርፑል ድል ቀንቷቸዋል
Sep 10, 2026 235
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ)፦ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሊግ ምዕራፍ ጨዋታዎች ማምሻውን ተካሄደዋል። በፓርክ ደ ፕሪንስ በተካሄደው ጨዋታ ፒኤስጂ ስሎቫን ብራቲስላቫን 6 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ፌራን ቶሬስ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። የወቅቱ የባሎን ዶር ሽልማት ባለቤት ኡስማን ዴምቤሌ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ፋቢያን ሩዊዝ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሱሌማን ካማራ የብራቲስላቫን ብቸኛ ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ባለሜዳው ፒኤስጂ ከፍተኛ ብልጫ ወስዷል። ባለፉት ሁለት የውድድር ዓመታት ዋንጫውን ያነሳው ፒኤስጂ ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን በድል ጀምሯል። በሌላኛው መርሐ ግብር አርሰናል ናፖሊን 1 ለ 0 አሸንፏል። በዲያጎ አርማንዶ ማራዶና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማርቲን ኦዴጋርድ በ75ኛው ደቂቃ ግቧን አስቆጥሯል። የባለፈው ዓመት የፍጻሜ ተፋላሚ አርሰናል የመጀመሪያ ድሉን አግኝቷል። ሊቨርፑል አትሌቲኮ ማድሪድን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዶምኒክ ስቦዝላይ እና አሌክሲስ ማካሊስተር የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ማርኮስ ሊዮሬንቴ ለአትሌቲ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ስፓርቲንግ ሊዝበን ጋላታሳራይን 3 ለ 1 ረትቷል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ባርሴሎና ፌይኖርድን 5 ለ 1 ሲረታ፣ ስቱትጋርት ቫይኪንግን 3 ለ 1 አሸንፏል።
ቼልሲ በካራባኦ ካፕ ወደ ቀጣዩ ዙር አለፈ
Sep 10, 2026 177
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ካራባኦ ካፕ ሶስተኛ ዙር መርሐ ግብር ቼልሲ ከመመራት ተነስቶ ሊድስ ዩናይትድን 6 ለ 3 አሸንፏል። ማምሻውን በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኮል ፓልመር (አንዱ በፍጹም ቅጣት ምት) እና ዳኒ ዌልቤክ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን አስቆጥረዋል። ፔድሮ ኔቶ እና ቫለንቲን ባርኮ ቀሪዎቹን ግቦች ለሰማያዊዎቹ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ታሪክ ሙሃሬሞቪች፣ ብሬንደን አሮንሰን እና ዶምኒክ ካልቨርት-ሉዊን ለሊድስ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሊድስ ዩናይትድ በመጀመሪያ አጋማሽ አጋማሽ 2 ለ 0 በመምራት ከሜዳ ቢወጣም ቼልሲ ከእረፍት መልስ ስድስት ግቦችን በማስቆጠር ውጤቱን ቀልብሷል። ዘጠኝ ጎሎች በተቆጠሩበት ጨዋታ ቼልሲ በሊጉ በአርሰናል ካጋጠመው ሽንፈት በኋላ ወደ ድል መንገድ ተመልሷል። ውጤቱን ተከትሎም ቼልሲ ወደ አራተኛ ዙር አልፏል። ሊድስ ዩናይትድ የካራባኦ ካፕ ጉዞው ሶስተኛ ዙር ላይ ተገቷል።
የ2019 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በሰባት ስታዲየሞች ይደረጋል
Sep 9, 2026 177
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4 /2018 (ኢዜአ)፦ የ2019 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በተመረጡ ሰባት ስታዲየሞች እንደሚካሄድ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታወቀ። የሊጉ ጨዋታዎች የእጣ ማውጣት ስነ ስርዓት መስከረም 7 ቀን 2019 ዓ.ም ይከናወናል። መስከረም 30 የሚጀምረው የ2019 ዓ.ም የሊጉ ውድድር በተመረጡ ሰባት ሜዳዎች እና በተዘጋጁ ስድስት ቋቶች በሚወጣው እጣ መሰረት የውድድር ዓመቱ መርሃ ግብር ይዘጋጃል። አዲስ አበባ ስታዲየም፣ አዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ ስታዲየም፣ ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ባህርዳር አለም አቀፍ ስታዲየም፣ሀላባ ስታዲየም፣ ሆሳዕና አብዩ ኤርሳሞ ስታዲየም እና አርባምንጭ ዩንቨርሲቲ አባያ ካምፓስ ስታዲየም ውድድሩ የሚካሄድባቸው ሜዳዎች ናቸው። በውድድሩ ላይ 18 ክለቦች እንደሚሳተፉ የሊጉ አክሲዮን ማህበር መረጃ ያመለክታል።