ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ቼልሲ የውድድር ዓመቱን በድል ጀምሯል
Aug 24, 2026 78
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ ግብር ቼልሲ ፉልሃምን 3 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በክራቫን ኮቴጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆአኦ ፔድሮ፣ ሞርጋን ሮጀርስ እና ኮል ፓልመር የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ጆአኦ ፔድሮ በ31ኛው ሴኮንድ ያስቆጠረው የዓመቱ ፈጣን ጎል ሆኖ ተመዝግቧል። ጆሹዋ ኪንግ እና ጎንዛሎ ጋርሺያ የፉልሃምን ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በ117 ሚሊዮን ፓውንድ ከአስቶንቪላ ወደ ቼልሲ የተዘዋወረው ሞርጋን ሮጀርስ በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታው ጎል አስቆጥሯል። ከሪያል ማድሪድ ፉልሃምን የተቀላቀለው ጎንዛሎ ጋርሺያም የመጀመሪያ የሊግ ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው እጅግ አዝናኝና በርካታ የግብ እድሎች የተፈጠሩበት ነበር። የቼልሲው አሰልጣኝ ዣቪ አሎንሶ በመጀመሪያ ጨዋታው ድል ቀንቶታል። በአንጻሩ አዲሱ የፉልሃም አዲሱ አሰልጣኝ አርቫሎ አርቤሎአ በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታቸው ሽንፈት አስተናግዷል። ጨዋታውን ተከትሎ የመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር ተጠናቋል። የሁለተኛ ሳምንት የሊጉ ጨዋታዎች ከአርብ ነሐሴ 22 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳሉ።
ኢትዮጵያ የ2028ቱን የአፍሪካ ዋንጫ ለማስተናገድ ጥያቄዋን ያቀረበችበትን ሰነድ ለካፍ አስገባች
Aug 24, 2026 129
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ የ2028ቱን የአፍሪካ ዋንጫ ለማስተናገድ ጥያቄዋን ያቀረበችበትን ሰነድ (Bid Document) ለአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስገብታለች። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከመንግሥት ጋር በጋራ አስፈላጊ ዶክመንቶችን ያካተተ ሰነድ (BID HAND BOOK) ለካፍ ማስገባቱን አመልክቷል። ይህም ኢትዮጵያ ታላቅ አህጉራዊ የእግር ኳስ ድግስ ለአራተኛ ጊዜ በስኬት ለማስተናገድና በአፍሪካ እግር ኳስ ያላትን ጉልህ ታሪክ ዳግም ለማደስ ዝግጁነቷን ማረጋገጧን ፌዴሬሽኑ አስታውቋል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ሽንፈትን አስተናገደ
Aug 24, 2026 91
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ የምድብ ሁለት መርሐ ግብር የዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አግነስ ናቡኬንያ በ11ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ግቧን አስቆጥራለች። በአሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው የሚመራው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሽንፈቱን ተከትሎ ወደ ግማሽ ፍጻሜ የማለፍ እድሉ አጣብቂኝ ውስጥ ገብቷል። ንግድ ባንክ በመጀመሪያው የምድብ ጨዋታው የጅቡቲውን ኡጄኮን 11 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ቡድኑ ወደ ግማሽ ፍጻሜው ለማለፍ በመጨረሻው የምድብ ጨዋታ ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስን በኡጄኮ መሸነፍ ይኖርበታል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ረቡዕ ነሐሴ 2018 ዓ.ም በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም ይካሄዳል። ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ በጨዋታው ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ያልፋል። የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ከነሐሴ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በሩዋንዳ ኪጋሊ እየካሄደ ይገኛል። በውድድሩ ላይ 10 ክለቦች በሶስት ምድብ ተከፍለው ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል። የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ውድድሩን ያሸነፈው ክለብ ዞኑን ወክሎ በሻምፒዮንስ ሊጉ መሳተፉን ያረጋግጣል። የሴካፋ ማጣሪያ እስከ ነሐሴ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
በሳምንቱ መጨረሻ በተካሄዱ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ድል ቀንቷቸዋል
Aug 24, 2026 138
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በሳምንቱ መጨረሻ በተለያዩ ሀገራት በተካሄዱ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድሮች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች አሸንፈዋል። በሰሜን አየርላንድ ላርን ከተማ በተካሄደው የ“Antrim Coast Road Race” ውድድር፣ ዘንድሮ አዲስ በተካተተው የአምስት ኪሎ ሜትር ዘርፍ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የበላይነቱን ይዘዋል። በሴቶች 5 ኪሎ ሜትር ውድድር አትሌት አይናዲስ መብራቱ ርቀቱን በ14 ደቂቃ ከ51 ሴኮንድ በመጨረስ አሸንፋለች። የወንዶቹን 5 ኪሎ ሜትር ውድድር አትሌት ኤርሚያስ ግርማ በ13 ደቂቃ ከ50 ሴኮንድ በድል አጠናቋል። በዚሁ ውድድር በሴቶች 21 ኪሎ ሜትር ግማሽ ማራቶን አትሌት ግርማዊት ገብረእግዚአብሔር 1 ሰዓት ከ6 ደቂቃ ከ12 ሴኮንድ አንደኛ ወጥታለች። አትሌት ውዴ ከፍያለው 1 ሰዓት ከ7 ደቂቃ ከ12 ሴከንድ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በወንዶች ግማሽ ማራቶን አትሌት ይስማው ድሉ 1 ሰዓት 1 ደቂቃ ከ5 ሴኮንድ አምስተኛ ወጥቷል። በሌላ በኩል፣ በፓላንድ ሲሊሲያ ዳይመንድ ሊግ ውድድር ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ድል ቀንቷቸዋል። በወንዶች 3000 ሜትር መሰናክል አትሌት ገመቹ ጎዳና ርቀቱን በ8 ደቂቃ ከ2 ሴኮንድ አሸናፊ ሆኗል። በሴቶች 1500 ሜትር አትሌት ፅጌ ዱጉማ 3 ደቂቃ ከ55 ሴከንድ በአስደናቂ አጨራረስ ድል ተቀዳጅታለች። በርቀቱም የዓመቱን ፈጣን ሰዓት አስመዝግባለች። በሴቶች 5000 ሜትር አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ ርቀቱን በ14 ደቂቃ ከ54 ሴከንድ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቋን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል።
ቼልሲ ከፉልሃም ጋር ይጫወታል
Aug 24, 2026 127
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 18 /2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ፉልሃም ከቼልሲ በክራቨን ኮቴጅ ስታዲየም ይጫወታሉ። ፉልሃም ባለፈው የውድድር ዓመት በ52 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው። እ.አ.አ በ2025/26 የውድድር ዓመት ደካማ ብቃት ያሳየው ቼልሲ በ52 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀ ሲሆን ከአውሮፓ ውድድሮች ውጪ መሆኑም አይዘነጋም። ቼልሲ የ44 ዓመቱ ዣቪ አሎንሶን፣ ፉልሃም በበኩሉ የ43 ዓመት አልቫሮ አርቤሎአን በአሰልጣኝነት መሾማቸው ይታወቃል። ሁለቱ ስፔናዊ አሰልጣኞች የመጀመሪያ ጨዋታቸውን ዛሬ ያደርጋሉ። በሊቨርፑል፣ ሪያል ማድሪድ እና ስፔን ብሔራዊ ቡድን አብረው የተጫወቱት አሎንሶ እና አርቤሎአ በአሰልጣኝነት ዳግም ተገናኝተዋል። ሁለቱ የለንደን ክለቦች ከዚህ ቀደም በፕሪሚየር ሊጉ 38 ተገናኝተው ቼልሲ 23ቱን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ፉልሃም አራት ጊዜ ድል ሲቀናው በቀሪ 11 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ቼልሲ በ38ቱ ጨዋታዎች ላይ 61 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ፉልሃም 28 ግቦችን አስቆጥሯል። ሁለቱ ክለቦች ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ የተገናኙት እ.አ.አ ጃንዋሪ 2026 ላይ ሲሆን በክራቫን ኮቴጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፉልሃም 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ፉልሃም በከተማ ተቃናቃኙ ላይ ተከታታይ የሊግ ድል ለማስመዝገብ ይጫወታል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የመጨረሻ የምድብ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል
Aug 24, 2026 129
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ የምድብ ሁለት መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ጋር ዛሬ ጨዋታውን ያከናውናል። ጨዋታው ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከትናንት በስቲያ ባደረገው የመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ የጅቡቲውን ኡጄኮን 11 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ቡድኑ በጨዋታው ላይ ፍጹም የበላይነትን ወስዷል። በአሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው የሚመራው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፈ ለግማሽ ፍጻሜ ያልፋል። በአንጻሩ የምድቡን የመጀመሪያ ጨዋታ የሚያደርገው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይፋለማል። ሁለቱ ክለቦች እ.አ.አ በ2024 በአዲስ አበባ በተካሄደው የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ማጣሪያ በግማሽ ፍጻሜ ተገናኝተው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። ንግድ ባንክ በወቅቱ የማጣሪያ ውድድሩን በማሸነፍ በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመጀመሪያ ጊዜ መሳተፉ የሚታወስ ነው። የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ከነሐሴ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በሩዋንዳ ኪጋሊ እየካሄደ ይገኛል። በውድድሩ ላይ 10 ክለቦች በሶስት ምድብ ተከፍለው ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የማጣሪያ ውድድሩን ካሸነፈ በሻምፒዮንስ ሊጉ ለሁለተኛ ጊዜ መሳተፉን ያረጋግጣል። የሴካፋ ማጣሪያ እስከ ነሐሴ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በ2026 የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ ለመሳተፍ 36 ክለቦች በስድስት አህጉራዊ ዞኖች ተከፍለው የማጣሪያ ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል። በአህጉራዊ ቀጣናዎች በሚደረጉ ማጣሪያዎች አሸናፊ የሆኑ ክለቦች፣ የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ የሞሮኮው ኤኤስ ፋር እና ውድድሩን የሚያዘጋጀው ሀገር ተወካይ ጨምሮ ስምንት ቡድኖች በዋናው ውድድር ላይ እንደሚሳተፉ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል። የ2026 የካፍ የሴቶች ቻምፒየንስ ሊግ ዋና ውድድር አዘጋጅ ሀገር በቅርቡ በአወዳዳሪው አካል ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
ኒውካስትል ዩናይትድ እና ሊቨርፑል ነጥብ ተጋሩ
Aug 23, 2026 827
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 17/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት ጨዋታ ኒውካስትል ዩናይትድ እና ሊቨርፑል ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶኒ ኢላንጋ እና ጆ ዊሎክ ለኒውካስትል ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኮዲ ጋፕኮ እና ዶምኒክ ስቦዝላይ ለሊቨርፑል ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ስቦዝላይ በ99ኛ ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠረው ጎል ሊቨርፑልን አቻ አድርጓል። ኒውካስትል በማትያስ ጃይልስ፣ ሊቨርፑል በአንዶኒ ኢራኦላ በመጀመሪያ ጨዋታቸው አንድ ነጥብ አሳክተዋል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ ጨዋታዎች ማንችስተር ሲቲ ቦርንማውዝን 2 ለ 1፣ ብራይተን አስቶንቪላን 4 ለ 0 አሸንፈዋል።
ማንችስተር ሲቲ ድል ቀንቶታል
Aug 23, 2026 769
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 17/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር ማንችስተር ሲቲ ከመመራት ተነስቶ ቦርንማውዝን 2 ለ 1 አሸንፏል። በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማርከስ ታቫርኒየር በ26ኛው ደቂቃ የየቦርንማውዝ የመሪነትን ጎል አስቆጥሯል። የሲቲ ተከላካይ መስመር ድክመት ለግቡ መቆጠር ምክንያት ሆኗል። ማርክ ጌሂ በ84ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፈው ጎል ሲቲ አቻ ሆኗል። ጆሽኮ ግቫርዲዮል በ92ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ ቡድኑን አሸናፊ አድርጓል። ባለሜዳው ማንችስተር ሲቲ በጨዋታው ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። አዲሱ የሲቲ አሰልጣኝ ኤንዞ ማሬስካ በመጀመሪያ ጨዋታቸው ድል ቀንቷቸዋል። በአሜክስ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ብራይተን አስቶንቪላን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ጃክ ሂንሺልውድ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ማክሲም ዲ ካይፐር እና የአስቶንቪላው ቪክቶር ሊንድሎፍ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የአስቶንቪላው ጆአኦ ጎሜዝ በ40ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ወጥቷል። የወቅቱ የዩሮፓ ሊግ አስቶንቪላ አብዛኛውን የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በ10 ተጫዋች መጫወቱ ለብራይተን ከፍተኛ ብልጫ መውሰድ ምክንያት ሆኗል። ከደቂቃዎች በኋላ 12 ሰዓት ከ30 ላይ ኒውካስትል ዩናይትድ ከሊቨርፑል በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ይጫወታሉ።
አትሌት ዮሚፍ ቀጀልቻ የዓለም የግማሽ ማራቶን ሪከርድን ሰበረ
Aug 23, 2026 183
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 17/ 2018 (ኢዜአ) ፦ኢትዮጵያዊው አትሌት ዮሚፍ ቀጀልቻ በቦነስ አይረስ በተካሄደው ውድድር የግማሽ ማራቶን ሪከርድ ሰብሯል። የሩጫ ታሪክን እየፃፈ የሚገኘው አትሌት ዮሚፍ ርቀቱን በ56 ደቂቃ ከ51 ሰከንድ በማጠናቀቅ አዲስ የዓለም ሪከርድ አስመዝግቧል። በዚህም አትሌት ዮሚፍ ዩጋንዳዊው ጃኮብ ኪፕሊሞ ከዚህ በፊት አስመዝግቦት የነበረውን 57 ደቂቃ ከ20 ሴኮንድ የዓለም ሪከርድ በ29 ሴከንዶች በማሻሻል የርቀቱ የዓለም ፈጣን አትሌት መሆኑን አረጋግጧል።
ማንችስተር ሲቲ ከቦርንማውዝ፣ ኒውካስትል ከሊቨርፑል፡ ማን ያሸንፋል?
Aug 23, 2026 248
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 17/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬም ቀጥሎ ይካሄዳል። ከቀኑ 10 ሰዓት ማንችስተር ሲቲ ከቦርንማውዝ በኢትሃድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ከአሰልጣኝ ፔፕ ጋርዲዮላ የ10 ዓመታት ስኬታማ ቆይታ በኋላ፣ ማንችስተር ሲቲ በኤንዞ ማሬስካ አዲስ ምዕራፍ ይጀምራል። የ46 ዓመቱ ጣልያናዊ የመጀመሪያ የውድድር ጨዋታቸውን ዛሬ ከቦርንማውዝ ጋር ያደርጋሉ። በአንጻሩ አንዶኒ ኢራኦላን ወደ ሊቨርፑል የሸኘው ቦርንማውዝ የ49 ዓመቱ ጀርመናዊ ማርኮ ሮስን በአሰልጣኝነት መሾሙ ይታወቃል። ቦርንማውዝ ከባለፈው የውድድር ዓመት የቀጠለውን በሊጉ የ18 ጨዋታዎች ያለመሸነፍ አስደናቂ ጉዞ ለማስጠበቅ ወደ ሜዳ ይገባል። ሁለቱ ቡድኖች ባለፈው የውድድር ዓመት በ37ኛው ሳምንት ያደረጉት ጨዋታ በአንድ አቻ ውጤት መጠናቀቁ ይታወሳል። ይህም የማንችስተር ሲቲን የዋንጫ ፉክክር ያበቃና የአርሰናልን የሊግ ሻምፒዮንነት ያረጋገጠ ነበር። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሃ ግብር ኒውካስትል ዩናይትድ ከሊቨርፑል ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ላይ በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኒውካስትል ዩናይትድ ባለፈው የውድድር ዓመት በ49 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው። ተጋጣሚው ሊቨርፑል በ60 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። ሁለቱ ቡድኖች አምና ጥሩ የሚባል ጊዜ አላሰለፉም። ይህን ተከትሎም ሊቨርፑል አርን ስሎትን፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ኤዲ ሃውን አሰንብተዋል። ሊቨርፑል አንዶኒ ኢራኦላን በአሰልጣኝነት ሲሾም ኒውካስትል ማቲያስ ጃይስልን ቀጥሯል። ቡድኖቹ አዲሱን የውድድር ዓመት በአዲስ አሰልጣኝ ይጀምራሉ። ብራይተን ከአስቶንቪላ ከቀኑ 10 ሰዓት በአሜክስ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባለፈው የውድድር ዓመት ብራይተን በ53 ነጥብ ስምንተኛ፣ አስቶንቪላ በ65 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። የወቅቱ የዩሮፓ ሊግ አሸናፊ አስቶንቪላ በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታ ጠንካራ ፈተና እንደሚገጥመው ይጠበቃል። ብራይተን ዓመቱን በድል ለመጀመር ይጫወታል።
የ76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ስብሰባ ተሳታፊዎች ጤናማ የአኗኗር ዘይቤን ማስፋፋት ዓላማ ያደረገ የእግር ጉዞ እያደረጉ ነው
Aug 23, 2026 141
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 17/2018 (ኢዜአ)፦ የ76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ስብሰባ ተሳታፊዎች ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመከላከልና ጤናማ የአኗኗር ዘይቤን ለማስፋፋት ዓላማ ያደረገ የጋራ የእግር ጉዞ እያካሄዱ ነው። የእግር ጉዞው ከአድዋ ድል መታሰቢያ ተነስቶ በከተማዋ የእግረኛ መንገድ በመከተል መስቀል አደባባይ ላይ የሚጠናቀቅ ይሆናል። የእግር ጉዞው “ንግግርን ወደ ተግባር” (Walk the Talk) በሚል መሪ ሐሳብ እየተካሄደ ነው። በእግር ጉዞው የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባን ጨምሮ የአፍሪካ ሀገራት የጤና ሚኒስትሮች፣ ከፍተኛ የመንግሥት ሥራ ኃላፊዎች፣ የዓለም ጤና ድርጅት አመራሮች፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኮማንደር ስለሺ ስህን እንዲሁም ሌሎች ታዋቂ አትሌቶች ተሳትፈዋል። የጤና አመራሮቹ በጉዞው በመሳተፍ የአካል እንቅስቃሴ እንደ ስኳር በሽታ፣ የደም ግፊትና የልብ ሕመም ያሉ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን መከላከል ያለውን ጠቀሜታ በተግባር ለማሳየት ነው። የእግር ጉዞው የጤና ፖሊሲ ውሳኔዎችን ወደ ተጨባጭ ተግባር ለመቀየርና በአፍሪካ ሕዝቦች መካከል ጤናማ የአኗኗር ዘይቤን ለማስፋፋት ያለመ መልዕክት ለማስተላለፍም ነው። የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ 76ኛ ስብሰባ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ሲሆን፣ በአፍሪካ የጤና ስልቶችና የቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ውይይት ያደርጋል።
ብሬትንፎርድ ቶተንሃም ሆትስፐርስን አሸንፏል
Aug 22, 2026 345
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር ብሬንትፎርድ ቶተንሃም ሆትስፐርስን 3 ለ 0 ረትቷል። ማምሻውን በጂቴክ ኮሙኒቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኪን ሉዊስ-ፖተር፣ ቫይታሊ ጃኔሌት እና ማይክል ካዮዴ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የብሬንትፎርዱ አጥቂ ኢጎር ቲያጎ በ55ኛው ደቂቃ ፍጹም ቅጣት ምት ስቷል። ባለሜዳው ብሬንትፎርድ ኢላማቸውን የጠበቁ ሙከራዎችን ወደ ግብ በመቀየር ውጤታማ ነበር። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በጨዋታው ላይ ደካማ እንቅስቃሴ ያደረገ ሲሆን ግልጽ የግብ እድሎችን መፍጠር ተስኖታል። ብሬንትፎርድ አዲሱን የውድድር ዓመት በድል ጀምሯል። በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት በርካታ ገንዘብ ያፈሰሰው ቶተንሃም በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታ ሽንፈት አስተናግዷል።
ኤቨርተን ፣ ሊድስ ዩናይትድ እና ኤፕስዊች ታውን ድል ቀንቷቸዋል
Aug 22, 2026 340
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የአንደኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች መካሄዳቸውን ቀጥለዋል። ማምሻውን በሂል ዲክንሰን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኤቨርተን ክሪስታል ፓላስን 2 ለ 0 ረትቷል። ኪርናን ዴውስበሪ-ሆል እና ቲዬርኖ ባሪ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ባለፈው የውድድር ዓመት 13ኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀው ኤቨርተን በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታ ድል ቀንቶታል። ተጋጣሚው ክሪስታል ፓላስ ዓመቱን በሽንፈት ጀምሯል። በሲቲ ግራውንድ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ሊድስ ዩናይትድ ኖቲንግሃም ፎረስትን 1 ለ 0 አሸንፏል። አንቶን ስታች የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በፖርትማን ሮድ በተካሄደው ጨዋታ አዲስ አዳጊው ኤፕስዊች ታውን ሰንደርላንድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ኤመርሰን እና ጃክ ክላርክ ለኤፕስዊች ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኒልሰን አንጉሎ ለሰንደርላንድ ጎሏን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ብሬንትፎርድ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ በጂቴክ ኮሙኒቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቀን ላይ በተደረገ መርሐ ግብር አዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ ማንችስተር ዩናይትድን 2 ለ 0 አሸንፏል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የማጣሪያ ጉዞ በድል ጀምሯል
Aug 22, 2026 168
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን የምድብ ሁለት የማጣሪያ መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የጅቡቲው ኡጄኮን 11 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ እሙሽ ዳንኤል አምስት ግቦችን አስቆጥራለች። ረድኤት አስረሳኸኝ እና ሊዲያ እያሱ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥሩ እፀገነት ግርማ እና ታሪኳ ዴቢሶ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በብርሃኑ ግዛው የሚመራው ንግድ ባንክ በጨዋታው ፍጹም የጨዋታው የበላይነትን ወስዷል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለተኛ የምድብ ጨዋታውን ማክሰኞ ነሐሴ 19 ቀን 2018 ዓ.ም ከዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ጋር ያደርጋል። ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ ለሁለተኛ ጊዜ ለመሳተፍ የማጣሪያ ጉዞውን በአሸናፊነት ማጠናቀቅ ይኖርበታል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በውድድሩ ላይ እየተሳተፈ የሚገኘው የ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አሸናፊ መሆኑን ተከትሎ ነው። በሩዋንዳ ኪጋሊ አስተናጋጅነት የሚካሄደው የሴካፋ ዞን የማጣሪያ ውድድር ትናንት መጀመሩ ይታወቃል። የማጣሪያ ውድድሩ እስከ ነሐሴ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
ማንችስተር ዩናይትድ በአዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ ሽንፈት አስተናገደ
Aug 22, 2026 163
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር ሁል ሲቲ ማንችስተር ዩናይትድን 2 ለ 0 አሸንፏል። በኤምኬኤም ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሴሚ አጃይ እና ኖቤል ሜንዲ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ባለሜዳው ሁል ሲቲ በመጀመሪያው አጋማሽ ሁለቱንም ግቦች አስቆጥሯል። ቡድኑ ውጤቱን አስጠብቆ ወጥቷል። ማንችስተር ዩናይትድ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ወደ ጨዋታው ለመመለስ የሚያስችሉትን ግቦች ማስቆጠር አልቻለም። ከዘጠኝ ዓመት በኋላ ወደ ሊጉ የተመለሰው ሁል ሲቲ ሳይጠበቅ ወሳኝ ድል አሳክቷል። ሁል ሲቲ በሊጉ ለመጀመሪያ ጊዜ ዩናይትድን አሸንፏል። ማንችስተር ዩናይትድ ያልተጠበቀ ሽንፈት አስተናግዷል።
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሴቶች ቡድን የካፍ የሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የማጣሪያ ጉዞ
Aug 22, 2026 139
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 16/2018 (ኢዜአ)፦ ስድስተኛው የካፍ የሻምፒዮንስ ሊግ በ2019 ዓ.ም ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ ለመሳተፍ በስድስት ዞኖች 36 ክለቦች የማጣሪያ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የምስራቅ እና መካከለኛው አፍሪካ (ሴካፋ) ከዞኖቹ መካከል አንዱ ሲሆን በዚህ ዞን ኢትዮጵያን ወክሎ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሴቶች ክለብ ጨምሮ 10 ክለቦች የሻምፒዮንስ ሊጉን ቦታ ለማግኘት ይፋለማሉ። በሩዋንዳ ኪጋሊ አስተናጋጅነት የሚካሄደው የሴካፋ ዞን የማጣሪያ ውድድር ትናንት ጅማሮውን አግኝቷል። በማጣሪያ ውድድሩ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች እግር ኳስ ክለብ በምድብ ሁለት ከዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ እና ከጅቡቲው ኡጄኮ ክለብ ጋር ተደልድሏል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የመጀመሪያ ጨዋታውን ዛሬ ከጅቡቲው ኡጄኮ ክለብ ጋር ከቀኑ ስምንት ሰዓት ላይ በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም ያደርጋል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች እግር ኳስ ክለብ በማጣሪያ ውድድሩ የሚሳተፈው የ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አሸናፊ መሆኑን ተከትሎ ነው። በአሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው የሚመራው ንግድ ባንክ የሴካፋ ዞን አህጉራዊ ማጣሪያ ከተጀመረበት ከእ.አ.አ 2021 አንስቶ ተሳትፎ ሲያደርግ ቆይቷል። እ.አ.አ 2021 እና በ2023 ውድድሮች እስከ ፍጻሜ ደርሶ በሁለተኝነት ያጠናቀቀው ንግድ ባንክ፣ እ.አ.አ በ2024 በአዲስ አበባ በተካሄደው የሴካፋ ማጣሪያ ግን ህልሙን እውን አድርጓል። ቡድኑ በፍጻሜው የኬንያ ፖሊስ ቡሌትስን 1 ለ 0 በማሸነፍ የሴካፋ ዞን ቻምፒየን በመሆን፣ በታሪክ የመጀመሪያው በካፍ የሴቶች ቻምፒየንስ ሊግ ዋናው የስምንት ቡድኖች ውድድር ላይ የተሳተፈ የኢትዮጵያ ክለብ መሆን ችሏል። በሞሮኮ በተካሄደው ዋና ውድድር ከናይጄሪያው ኤዶ ኩዊንስ፣ ከደቡብ አፍሪካው ማሜሎዲ ሳንዳውንስ እና ከግብጹ ማሳር ጋር በምድብ ድልድል ተደልድሎ ተጫውቷል። ንግድ ባንክ በሶስቱም ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዶ ከምድቡ ማለፍ አልቻለም። በሴናፍ ዋቁማ አማካኝነት ታሪካዊ የመጀመሪያ ግቡን የግብጹ ማሳር ላይ ያስቆጠረ ሲሆን ከካፍ የ150 ሺህ ዶላር የተሳትፎ ክፍያ ማግኘት ችሏል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለተኛ የምድብ ጨዋታውን ማክሰኞ ነሐሴ 19 ቀን 2018 ዓ.ም ከዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ ጋር ያደርጋል። ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ ለሁለተኛ ጊዜ ለመሳተፍ የማጣሪያ ጉዞውን በአሸናፊነት ማጠናቀቅ ይኖርበታል። የማጣሪያ ውድድሩ እስከ ነሐሴ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በስድስት አህጉራዊ ቀጣናዎች በሚደረጉ ማጣሪያዎች አሸናፊ የሆኑ ክለቦች፣ የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ የሞሮኮው ኤኤስ ፋር እና ውድድሩን የሚያዘጋጀው ሀገር ተወካይ ጨምሮ ስምንት ቡድኖች በዋናው ውድድር ላይ እንደሚሳተፉ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል። የ2026 የካፍ የሴቶች ቻምፒየንስ ሊግ ዋና ውድድር አዘጋጅ ሀገር በቅርቡ በአወዳዳሪው አካል ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል።
ማንችስተር ዩናይትድ ከአዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ ጋር ይጫወታል
Aug 22, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 16/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አምስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 8 ሰዓት ከ30 ላይ ሁል ሲቲ ከማንችስተር ዩናይትድ በኤምኬኤም ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሁል ሲቲ ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ ዳግም ወደ ሊጉ መመለሱ ይታወቃል። ክለቡ ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ ላይ የተወዳደረው እ.አ.አ 2016/17 ነበር። በማይክል ካሪክ የሚመራው ማንችስተር ዩናይትድ ባለፈው የውድድር ዓመት በ71 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው። በዘንድሮው የውድድር ዓመትም በጥሩ ግስጋሴው ለመቀጠል በመክፈቻ ጨዋታ አዲስ አዳጊውን ክለብ ማሸነፍ ይጠበቅበታል። ሁለቱ ክለቦች ከዚህ ቀደም በሊጉ 10 ጊዜ ተገናኝተዋል። ማንችስተር ዩናይትድ በስምንቱ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ማንችስተር ዩናይትድ በ10ሩ ጨዋታዎች ላይ 22 ግቦችን ሲያስቆጥር ሁል ሲቲ ሰባትጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሁለቱ ክለቦች ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ የተገናኙት እ.አ.አ በ2017 ሲሆን በኦልትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ያለ ግብ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። ሁል ሲቲ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ በሊጉ ማንችስተር ዩናይትድን ለማሸነፍ ይፋለማል። በሌሎች መርሐ ግብሮች ኢፕስዊች ታውን ከሰንደርላንድ፣ ኤቨርተን ከክሪስታል ፓላስ እና ኖቲንግሃም ፎረስት ከሊድስ ዩናይትድ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ብሬንትፎርድ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ በጂቴክ ኮሚኒቲ ስታዲየም ይጫወታሉ።
ሻምፒዮኑ አርሰናል የዋንጫ ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን በድል ጀምሯል
Aug 21, 2026 380
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በ2026/27 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ መርሐ ግብር አርሰናል ኮቨንተሪ ሲቲን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ካይ ሃቫርትዝ፣ ቡካዮ ሳካ እና ማርቲን ኦዴጋርድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሃቫርትዝ በ15ኛው ደቂቃ የአዲሱን የውድድር ዓመት የመጀመሪያ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የኮቨንተሪው ካሌብ ይሬንቺ በ27ኛው ደቂቃ የመጀመሪያውን ቢጫ ካርድ ተመልክቷል። አርሰናል በጨዋታው ከፍተኛ ብልጫ ወስዷል። አዲስ አዳጊው ኮቨንተሪ ሲቲ የግብ እድሎችን መፍጠር ተስኖታል። ሻምፒዮኑ አርሰናል የዋንጫ ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን በድል ጀምሯል። አዲስ አዳጊው ኮቨንተሪ ሲቲ በመጀመሪያው ጨዋታ ሽንፈት አስተናግዷል። የፕሪሚየር ሊጉ የመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር እስከ ነሐሴ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የተወዳጁ እንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ አዲስ የውድድር ዘመን በሻምፒዮኑ አርሰናል እና ኮቨንተሪ ሲቲ ጨዋታ ይጀመራል
Aug 21, 2026 300
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ)፦ የ2026/27 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ጅማሮውን ያደርጋል። ምሽት አራት ሰዓት ላይ አርሰናል ከኮቨንተሪ ሲቲ ጋር በኤምሬትስ ስታዲየም ጨዋታውን ያደርጋል። አርሰናል የወቅቱ የፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮን ነው። ተጋጣሚው ኮቨንተሪ ሲቲ ከ25 ዓመታት በኋላ ወደ ፕሪሚየር ሊግ ተመልሷል። ሁለቱ ቡድኖች በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሲገናኙ የአሁኑ ለ19ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 18 ጨዋታዎች አርሰናል 10ሩን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ኮቨንተሪ ሲቲ ሦስት ጊዜ ሲያሸንፍ በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። አርሰናል በ18ቱ ጨዋታዎች ላይ 25 ጎሎችን ሲያስቆጥር ኮቨንተሪ ሲቲ 13 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሁለቱ ቡድኖች ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ የተገናኙት እ.አ.አ በ2001 ነበር። በወቅቱ ባደረጉት ጨዋታ አርሰናል በዴኒስ ቤርካምፕ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል። ኮቨንተሪ ሲቲ በዛው ዓመት ከሊጉ ወርዷል። ኮቨንተሪ በፍራንክ ላምፓርድ እየተመራ በሻምፒዮንሺፑ በ95 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ ከ25 ዓመታት በኋላ ወደ ፕሪሚየር ሊጉ ተመልሷል። በማይክል አርቴታ የሚመራው አርሰናል የሻምፒዮንነት ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን ከአዲስ አዳጊው ክለብ ጋር በሚያደርገው ጨዋታ ይጀምራል። ኮቨንተሪ ሲቲ በመጀመሪያው የሊግ ጨዋታው ከሊጉ የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ከባድ ፈተና ይጠብቀዋል። የ36 ዓመቱ ቶም ብራሞል የመክፈቻውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመራሉ። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሐ ግብር እስከ ነሐሴ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየም ለአህጉራዊ ውድድሮች ብቁ መሆኑ ከስፖርቱ ባለፈ ለቱሪዝም ዘርፍ ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው
Aug 20, 2026 252
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦ የባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየም ለአህጉራዊ ውድድሮች ብቁ መሆኑ ከስፖርት ባለፈ ለቱሪዝም ዘርፍ ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን የክልሉ ባህል ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ገለጸ። የባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየምን ለአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ውድድሮች ዝግጁ ለማድረግ ሰፊ የማሻሻያና የመልሶ ግንባታ ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸው ይታወቃል። የስታዲየሙን ለጨዋታ ዝግጁ መሆን ከውድድር ባለፈ በተለይም ለቱሪዝም ያለውን ፋይዳ በተመለከተ የአማራ ክልል ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አየለ አናውጤ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በማብራሪያቸውም የባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየም ለአህጉራዊ ውድድሮች ብቁ መሆኑ ከስፖርትም ባለፈ ለቱሪዝም ዘርፍ ማንሰራራት ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን አስረድተዋል። ከእግር ኳስ ውጭም በከተማዋ የውሃ ዋና፣ የአትሌቲክስ እና የብስክሌት ውድድሮችን ለማስፋት ምቹ ሁኔታዎች መኖራቸውን ነው የጠቆሙት ። በከተማዋ የተገነቡ እና በመገንባት ላይ ያሉ ባለ ኮከብ ሆቴሎች መኖራቸው የካፍ ባለሙያዎችን መስፈርት የሚያሟላ እና ለዘርፉ ዘላቂ እድገት አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም የስታዲየሙ ዝግጁነት ለሀገራዊ የስፖርት እድገት እንዲሁም ለስፖርት ቤተሰቡ እና ለብሔራዊ ቡድኑ ጭምር ትልቅ የምስራች መሆኑን ጠቅሰው ለቱሪዝም ዘርፉም ትልቅ አቅም ይሆናል ብለዋል። ስታዲየሙ የጨዋታ መስፈርቱን አሟልቶና ብቁ ሆኖ መገኘቱ ብሔራዊ ቡድኑ እና ክለቦች አህጉራዊ ጨዋታዎችን በሜዳቸውና በደጋፊዎቻቸው ፊት የመጫወት ዕድል አመቻችቷል።