ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
አርሰናል ከቼልሲ፡ የሳምንቱ ተጠባቂ የሊግ ጨዋታ
Sep 6, 2026 215
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር አርሰናል ከቼልሲ ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የለንደን ደርቢ ጨዋታ ምሽት 12፡30 ላይ በኤምሬትስ ስታዲየም ይካሄዳል። አርሰናል እና ቼልሲ በተመሳሳይ በስድስት ነጥብ፣ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ሶስተኛና አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። ባለሜዳው አርሰናል በሁለቱ የሊግ ጨዋታዎች አራት ግቦችን ሲያስቆጥር ምንም ግብ አላስተናገደም። ይህም የቡድኑን፣ በተለይም የተከላካይ መስመሩን ጥንካሬ የሚያሳይ ነው። ተጋጣሚው ቼልሲ በሁለት ጨዋታዎች ሰባት ግቦችን ከመረብ ሲያሳርፍ አምስት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቼልሲ የማጥቃት እንቅስቃሴው ጥሩ የሚባል ቢሆንም በተከላካይ ክፍሉ ላይ ያሉ ድክመቶችን ማረም ይኖርበታል። ሁለቱ የለንደን ተቀናቃኝ ክለቦች በሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ69ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 68 ጨዋታዎች አርሰናል በ28ቱ ድል ሲቀናው፣ ቼልሲ 20 ጊዜ አሸንፏል። በቀሪ 18 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በነዚህ ጨዋታዎች አርሰናል 97 ግቦችን ከመረብ ሲያሳርፍ፣ ቼልሲ በበኩሉ 85 ጎሎችን አስቆጥሯል። ባለፉት አምስት የሊግ ግንኙነታቸው አርሰናል በሶስቱ ሲያሸንፍ፣ በቀሪዎቹ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርተዋል። ቼልሲ ለመጨረሻ ጊዜ አርሰናልን በሊጉ ያሸነፈው እ.አ.አ በ2021 ነው። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ አርሰናል በአዲሱ የውድድር ዓመት ያደረጋቸውን ሁለት ጨዋታዎች በማሸነፍ ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን በጥሩ ሁኔታ ጀምሯል። ተጋጣሚው ቼልሲም ሁለቱን የሊግ ጨዋታዎች በድል በመወጣት መልካም ጅማሮ አድርጓል። በመሆኑም የሁለቱ የለንደን ክለቦች ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ41 ዓመቱ ክሪስ ካቫናግ ተጠባቂውን ፍልሚያ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኤቨርተን ከማንችስተር ዩናይትድ በሂል ዲኪንሰን ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኤቨርተን ከሁለት ጨዋታዎች ማግኘት የቻለው አንድ ነጥብ ብቻ ሲሆን፣ ተጋጣሚው ማንችስተር ዩናይትድ ሶስት ነጥብ አለው። ባለሜዳው ኤቨርተን በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ ወደ ሜዳ ይገባል። በሁለተኛው ሳምንት ኤፕስዊች ታውንን 5 ለ 2 የረታው ማንችስተር ዩናይትድ ደግሞ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይፋለማል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል።
አስቶንቪላ በሊጉ የመጀመሪያ ነጥቡን አገኘ
Sep 5, 2026 325
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 30/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሁል ሲቲ እና አስቶንቪላ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በኤምኬ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አስቶንቪላ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ባለሜዳው ሁል ኢላማቸውን የጠበቁ ሙከራዎችን በማድረግ የተሻለ ነበር። አስቶንቪላ በውድድር ዓመቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢላማቸውን የጠበቁ የግብ ሙከራዎችን አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ አዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ በሰባት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ በሊጉ ጥሩ አጀማመር አሳይቷል። አስቶንቪላ በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ነጥቡን ያገኘ ሲሆን 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። እስከ አሁን በሊጉ ምንም ግብ አላስቆጠረም። በአራተኛ ሳምንት ሁል ሲቲ ከቼልሲ፣ አስቶንቪላ ከኖቲንግሃም ፎረስት ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ዛሬ በሊጉ ከተደረጉ ሰባት ጨዋታዎች መካከል አምስቱ በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል።
ሲዳማ ቡና ከኤግሎንስ ጋር አቻ ተለያየ
Sep 5, 2026 208
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 30/2018 (ኢዜአ):- በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ የመጀመሪያ ዙር የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ሲዳማ ቡና እና የቻዱ ኤግሎንስ ጋር ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታው ማምሻውን በኢድሪስ ዴቢ ኢትኖ ስታዲየም ተካሄዷል። ሲዳማ ቡና ግብ ማስቆጠር ባይችልም መልካም የሚባል እንቅስቃሴ አድርጓል። የሁለቱ ክለቦች የመልስ ጨዋታ መስከረም 2 ቀን 2019 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ሲዳማ ቡና በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ በሁለተኛው ዙር ማጣሪያ ከሱዳኑ አል ሂላል እና ከብሩንዲው አይግል ኑዋር አሸናፊ ጋር ይጫወታል። ሁለቱም ክለቦች በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ ሲወዳደሩ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።
ማንችስተር ሲቲ ኮቨንተሪ ሲቲን በማሸነፍ በሊጉ መሪነት ቀጥሏል
Sep 5, 2026 208
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 30/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ማንችስተር ሲቲ ኮቨንተሪ ሲቲን 1 ለ 0 አሸንፏል። በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሊንግ ሃላንድ በ26ኛው ደቂቃ ግቧን አስቆጥሯል። የ26 ዓመቱ አጥቂ በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ሶስት አድርሷል። ባለሜዳው ማንችስተር ሲቲ በጨዋታው ላይ በተጋጣሚው ተፈትኗል። ተጋጣሚው ኮቨንተሪ ሲቲ ግብ ሊያስቆጥርባቸው የሚችልባቸውን ግልጽ እድሎችን አምክኗል። በ125 ሚሊዮን ፓውንድ ከቼልሲ ወደ ማንችስተር ሲቲ የተዘዋወረው ኤንዞ ፈርናንዴዝ በቋሚ አሰላለፍ ውስጥ በመግባት የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ በዘጠኝ ነጥብ በመሪነነቱ ቀጥሏል። ሶስተኛ ተከታታይ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኮቨንተሪ ሲቲ ያለ ምንም ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በአራተኛ ሳምንት ማንችስተር ሲቲ ከከተማ ተቀናቃኙ ማንችስተር ዩናይትድ ጋር የሚያደርገው የደርቢ ጨዋታ ከወዲሁ ተጠባቂ ነው። ኮቨንተሪ ሲቲ ከብራይተን ጋር የሚጫወት ይሆናል። በሌሎች መርሐ ግብሮች ክሪስታል ፓላስ ፉልሃምን 3 ለ 2 አሸንፏል። ብሬንትፎርድ ከሰንደርላንድ፣ ብራይተን ከሊድስ ዩናይትድ በተመሳሳይ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ኖቲንግሃም ፎረስት እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ሁል ሲቲ ከአስቶንቪላ በኤምኬኤም ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ኒውካስትል ዩናይትድ እና ቦርንማውዝ አቻ ተለያዩ
Sep 5, 2026 165
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 30/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት ጨዋታ ኒውካስትል ዩናይትድ እና ቦርንማውዝ ያደረጉት ጨዋታ ሁለት አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሃርቪ ባርንስ እና ጃኮብ ራምሴ ለኒውካስትል ግቦቹን አስቆጥረዋል። ማርከስ ታቫርኒየር እና የኒውካስትሉ ተከላካይ ማሊክጅ ቲያው በራሱ ላይ የቦርንማውዝን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጃኮብ ራምሴ በ88ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል ኒውካስትልን አቻ አድርጓል። ቦርንማውዝ በጨዋታው 2 ለ 0 መምራት ቢችልም ውጤቱን ማስጠበቅ አልቻለም። በመጀመሪያው አጋማሽ ቦርንማውዝ፣ በሁለተኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ኒውካስትል ብልጫ ወስደው ተጫውተዋል። ውጤቱን ተከትሎ ኒውካስትል በአምስት ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ቦርንማውዝ በበኩሉ በሁለት ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ እስከ አሁን በሊጉ ምንም ጨዋታ አላሸነፈም።
በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ሲዳማ ቡና ከኤግሎንስ ጋር ይጫወታል
Sep 5, 2026 189
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 30/2018 (ኢዜአ):- በ2026/27 የካፍ ሻምፒዮንስ የመጀመሪያ ዙር ቅድመ ማጣሪያ ሲዳማ ቡና ከቻዱ ኤግሎንስ ጋር ዛሬ ጨዋታውን ያደርጋል። ጨዋታው ከቀኑ 11 ሰዓት ከ30 ላይ በኢድሪስ ዴቢ ኢትኖ ስታዲየም ይካሄዳል። ሲዳማ ቡና በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ውድድር ላይ ለመሳተፍ የበቃው የ2018 ዓ.ም. የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮን መሆኑን ተከትሎ ነው። በ1999 ዓ.ም የተቋቋመው ሲዳማ ቡና በአህጉራዊ መድረክ ሲሳተፍ ለመጀመሪያ ጊዜ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። በያሬድ ገመቹ የሚመራው ሲዳማ ቡና ለማጣሪያ ጨዋታው በሃዋሳ ልምምዱን ሲያደርግ ቆይቶ በተያዘው ሳምንት ወደ ስፍራው አቅንቷል። ቡድኑ ስብስቡን ለማጠናከር በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት አዳዲስ ተጫዋቾችን አስፈርሟል፣ የተጫዋቾችንም ውል አድሷል። ቢኒያም በላይ፣ ውብሸት ክፍሌ፣ ኤፍሬም ታምራት፣ ይገዙ ቦጋለ እና ዩጋንዳዊው ካሊድ አውቾ ከፈረሙት ተጫዋቾች መካከል ይጠቀሳሉ። በተጨማሪም ሲዳማ ቡና የአምበሉን ያሬድ ባየህ፣ መስፈን ታፈሰ እና ደስታ ደሙን የመሳሰሉ የቁልፍ ተጫዋቾቹን ውል አራዝሟል። ተጋጣሚው ኤግሎንስ ባለፈው የውድድር ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደውን የቻድ ፕሪሚየር ሊግን ማሸነፉን ተከትሎ በአህጉራዊ መድረኩ ላይ ይሳተፋል። ኤግሎንስ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ሲሳተፍ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። እ.አ.አ በ2015 የተመሰረተው ኤግሎንስ የወቅቱ አሰልጣኝ አማን አዱም ቱኒያ ናቸው። የሊጉ ምርጥ ተጫዋች ተብሎ የተመረጠው አጥቂው ፋቢየን ጄዳኑም እና ምርጥ ግብ ጠባቂ የተባለው ቢርዌ ማንጋና የቡድኑ ቁልፍ ተጫዋቾች ናቸው። የሁለቱ ክለቦች የመልስ ጨዋታ መስከረም 3 ቀን 2019 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ሲዳማ ቡና በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ በሁለተኛው ዙር ማጣሪያ ከሱዳኑ አል ሂላል እና ከብሩንዲው አይግል ኑዋር አሸናፊ ጋር ይጫወታል።
የሊጉ መሪ ማንችስተር ሲቲ ከኮቨንተሪ ሲቲ ጋር ይጫወታል
Sep 5, 2026 166
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 30/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሰባት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በኢትሃድ ስታዲየም ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በሚካሄደው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ አዲስ አዳጊውን ኮቨንተሪ ሲቲ ያስተናግዳል። ባለሜዳው ማንችስተር ሲቲ በስድስት ነጥብ ሊጉን እየመራ ይገኛል። በሁለቱ የሊጉ ጨዋታዎች ሽንፈት ያስተናገደው ኮቨንተሪ ሲቲ ያለ ምንም ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። ክለቦቹ ከዚህ ቀደም 10 ጊዜ በሊጉ ተገናኝተው በተመሳሳይ አራት ጊዜ ድል ቀንቷቸዋል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ የተገናኙት እ.አ.አ በ2001ነው። በወቅቱ ባደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ክለቦቹ ከ25 ዓመታት በኋላ ዳግም በሊጉ ይገናኛሉ። ማንችስተር ሲቲ ካሸነፈ የሊጉን መሪነት የሚያጠናክር ሲሆን ኮቨንተሪ ሲቲ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ ይፋለማል። በሌላኛው መርሐ ግብር ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ኖቲንግሃም ፎረስት ከቶተንሃም ሆትስፐርስ በሲቲ ግራውንድ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኖቲንግሃም ፎረስት በአንድ ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ቶተንሃም ሆትስፐርስ ያለ ምንም ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሁለቱም ክለቦች በሊጉ የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። በዝውውር መስኮቱ ከ300 ሚሊዮን ፓውንድ በላይ ያወጣው ቶተንሃም ደካማ ጅማሮ ያሳየ ሲሆን በሊጉ የመጀመሪያ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይፋለማል። ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ሁል ሲቲ አስቶንቪላን በኤምኬኤም ስታዲየም ጨዋታውን ያከናውናል። አዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ በስድስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። አስቶንቪላ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁል ሲቲ በመልካም ጅማሮው ለመቀጠል አስቶንቪላ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። በሌሎች መርሐ ግብሮች ብሬንትፎርድ ከሰንደርላንድ፣ ፉልሃም ከክሪስታል ፓላስ እና ብራይተን ከሊድስ ዩናይትድ በተመሳሳይ 11 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ከቀኑ 8 ሰዓት ከ30 ኒውካስትል ዩናይትድ ከቦርንማውዝ በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ።
በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ሽንፈት አስተናገደ
Sep 5, 2026 178
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ):- በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ የመጀመሪያ ቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በሱዳኑ ሂላል አል-ሳሂል 2 ለ 1 ተሸንፏል። ማምሻውን በሩዋንዳ በሚገኘው ኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዋሊድ አል-ሻላ እና ፋሪስ ሞሂ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ካርሎስ ዳምጠው ለወልዋሎ ጎሏን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሜዳው ውጪ ወሳኝ ጎል አስቆጥሯል። የሁለቱ ክለቦች የመልስ ጨዋታ መስከረም 2 ቀን 2019 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ በሁለተኛ ዙር ከዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም እና ከሊቢያው አል አህሊ ትሪፖሊ አሸናፊ ጋር የሚጫወት ይሆናል። ቡድኑ በአህጉራዊው መድረክ ለመሳተፍ የበቃው በኢትዮጵያ ዋንጫ ፍጻሜ ሲዳማ ቡናን 2 ለ 0 አሸንፎ ሻምፒዮን መሆኑን ተከትሎ ነው። ወልዋሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ሲሳተፍ በክለቡ የ70 ዓመታት ታሪክ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።
በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሊቨርፑል የመጀመሪያ ድሉን አስመዘገበ
Sep 5, 2026 174
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 30/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት የመጀመሪያ መርሐ ግብር ሊቨርፑል ኤፕስዊች ታውንን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በፖርትማን ሮድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አሌክሳንደር ኢሳክ በስድስተኛውና በዘጠነኛው ደቂቃ ግቦቹን አስቆጥሯል። በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት እንደሚለቅ በስፋት ሲነገር የቆየው ኮዲ ጋፕኮ ኳሶቹን አመቻችቶ አቀብሏል። ሊቨርፑል ከሜዳው ውጪ ባደረው ጨዋታ የተሻለ ብቃት ያሳየ ሲሆን ተጨማሪ ጎሎች ማስቆጠር ይችል ነበር። ባለሜዳው ኤፕስዊች ታውን ወደ ሊቨርፑል የግብ ክልል የመድረስ አጋጣሚዎችን ቢያገኝም ግልጽ የግብ እድሎችን መፍጠር አልቻለም። በ106 ሚሊዮን ፓውንድ ከፒኤስጂ ወደ ሊቨርፑል የተዘዋወረው ብራድሊ ባርኮላ በ64ኛው ደቂቃ በቪክቶር ሙኞዝ ተቀይሮ በመግባት የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ ሊቨርፑል የውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ድሉን አግኝቷል። አዲስ አዳጊው ኤፕስዊች ታውን ተከታታይ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በአራተኛ ሳምንት ኤፕስዊች ታውን ከክሪስታል ፓላስ፣ ሊቨርፑል ከፉልሃም ይጫወታሉ። የሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር እስከ ጳጉሜን 1 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከአል ሂላል ጋር ይጫወታል
Sep 4, 2026 193
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ):- በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ የመጀመሪያ ቅድመ ማጣሪያ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሱዳኑ አል ሂላል ጋር የመጀመሪያ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል። ጨዋታው ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ በሩዋንዳ በሚገኘው ኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም ይካሄዳል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በአህጉራዊው መድረክ ለመሳተፍ የበቃው በኢትዮጵያ ዋንጫ ፍጻሜ ሲዳማ ቡናን 2 ለ 0 አሸንፎ ሻምፒዮን መሆኑን ተከትሎ ነው። ወልዋሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ሲሳተፍ በክለቡ የ70 ዓመታት ታሪክ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። በአሰልጣኝ ግርማ ታደሰ የሚመራው ወልዋሎ ለቅድመ ማጣሪያው ጨዋታው ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቷል። ካርሎስ ዳምጠው፣ በረከት ሳሙኤል፣ እዮብ አለማየሁ እና አህመድ ረሺድን ጨምሮ የተለያዩ ተጫዋቾችን በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት መስኮት በማስፈረም ስብስቡን አጠናክሯል። ክለቡ ካስፈረማቸው ተጫዋቾች ባሻገር የጌቱ ኃይለማርያም እና አፈወርቅ ኃይሉን ጨምሮ የሌሎች ተጫዋቾችን ውል አራዝሟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በ46 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ ይታወሳል። ተጋጣሚው አል ሂላል በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ሲሳተፍ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። የሱዳኑ ክለብ ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፈው እ.አ.አ በ2022/23 የውድድር ዓመት እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ። በአሰልጣኝ ናዲር ዛርግ አክላንድ የሚመራው አል ሂላል በአህጉራዊ ውድድሮች ላይ የረጅም ጊዜ የተሳትፎ ልምድ አለው። እ.አ.አ በ1937 የተመሰረተው አል ሂላል አንጋፋ የሚባል ክለብ ነው። የሁለቱ ክለቦች የመልስ ጨዋታ መስከረም 2 ቀን 2019 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈ በሁለተኛ ዙር ከዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም እና ከሊቢያው አል አህሊ ትሪፖሊ አሸናፊ ጋር የሚጫወት ይሆናል።
ሊቨርፑል በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ለማግኘት ከኤፕስዊች ታውን ጋር ይጫወታል
Sep 4, 2026 220
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 29/2018 (ኢዜአ):- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ መርሐ ግብር ዛሬ ይጀመራል። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ኤፕስዊች ታውን ከሊቨርፑል በፖርትማን ሮድ ስታዲየም ይጫወታሉ። ከሁለት የሊጉ ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ያገኘው ኤፕስዊች ታውን 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ሊቨርፑል በሁለት ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ሁለቱ ክለቦች በሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ13ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 12 ጨዋታዎች ሊቨርፑል ሰባት ጊዜ ሲያሸንፍ ኤፕስዊች ታውን ሁለት ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ሊቨርፑል በ12 ጨዋታዎች ላይ 26 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ኤፕስዊች ታውን ዘጠኝ ጎሎችን አስቆጥሯል። ክለቦቹ በፕሪሚየር ሊጉ ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ ጃንዋሪ 2025 ሲሆን በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሊቨርፑል 4 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ባለሜዳው ኤፕስዊች ታውን በሁለተኛ ሳምንት በማንችስተር ዩናይትድ ካጋጠመው የ5 ለ 2 ሽንፈት አገግሞ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። በሁለቱም የሊጉ ጨዋታዎች አቻ የወጣው ሊቨርፑል የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ ይፋለማል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ መርሐ ግብር እስከ ጳጉሜን 1 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ለ2018 የውድድር ዓመት ኮከቦች ሽልማት ሊያበረክት ነው
Sep 2, 2026 363
አዲስ አበባ ፣ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ) ፦ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለ2018 ዓ.ም የውድድር ዓመት ምርጦች ዕውቅና የመስጠት መርሐ ግብር ጳጉሜን 3 እንደሚያካሂድ አስታወቀ። በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ፣ የወንዶች ከፍተኛ ሊግ፣ የሴቶች ከፍተኛ ሊግ፣ የሊግ አንድ እና ከ20 ዓመት በታች ፕሪምየር ሊግ የ2018 የውድድር ዘመን ኮከብ ተጫዋች፣ ኮከብ አሰልጣኝ፣ ኮከብ ግብ ጠባቂ፣ ከፍተኛ ጎል አስቆጣሪ እንዲሁም ምስጉን ዳኛ እና ረዳት ዳኞች ሽልማት ይበረከታል። የሽልማት ስነ ሥርዓቱ የሚካሄድበት ቦታ በቀጣይ እንደሚገለጽ ፌዴሬሽኑ ገልጿል።
ማንችስተር ሲቲ የቼልሲውን ኤንዞ ፈርናንዴዝን ለማስፈረም ተስማማ
Sep 1, 2026 359
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦ ማንችስተር ሲቲ በዝውውር መስኮቱ ማብቂያ ቀን የቼልሲውን አማካይ ኤንዞ ፈርናንዴዝን በ125 ሚሊዮን ፓውንድ ለማስፈረም ከስምምነት ላይ ደርሷል። የ25 ዓመቱ አርጀንቲናዊ አማካይ ከቤንፊካ በ107 ሚሊዮን ፓውንድ ወደ ቼልሲ የተቀላቀለው እ.አ.አ በ2023 ነበር። ተጫዋቹ ቼልሲ ከፉልሃም ጋር ባደረገው የመጀመሪያ የፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ ላይ ተሰልፎ የነበረ ቢሆንም፣ ከሉተን ጋር በካራባኦ ካፕ እንዲሁም ከብራይተን ጋር በተደረገው የሊጉ መርሐ ግብር አልተጫወተም። ይህ ዝውውር ሊቨርፑል ባለፈው ዓመት በክረምቱ የዝውውር መስኮት ማጠናቀቂያ ቀን የኒውካስትል ዩናይትዱን አጥቂ አሌክሳንደር ኢሳክ ለማስፈረም ከከፈለው የእንግሊዝ ክብረ ወሰን ክፍያ እኩል መሆኑን ስካይ ስፖርትስ ዘግቧል። ፈርናንዴዝ ወደ ማንችስተር ሲቲ ማምራት እንደሚፈልግ ያሳወቀ ሲሆን፣ በኢትሃድ ከቀድሞው የቼልሲ አሰልጣኙ ኤንዞ ማሬስካ ጋር እንደገና ይገናኛል። ተጫዋቹ በቀጣይ ሰዓታት ውስጥ የሕክምና ምርመራዎችን አድርጎ ዝውውሩን ሙሉ በሙሉ ያጠናቅቃል ተብሎ ይጠበቃል። ቼልሲ አርጀንቲናውን አማካይ የሚተካ ሌላ ተጫዋች ለማስፈረም እየሰሩ ይገኛሉ። ክለቡ የሮማውን ማኑ ኮኔ እና የሞናኮውን ላሚን ካማራን ለመግዛት እየተንቀሳቀሰ ሲሆን በፕሪሚየር ሊጉ የሚገኙ ሌሎች አማካዮችንም እየተመለከተ ይገኛል።
አርሰናል ተከታታይ ድሉን አስመዘገበ
Sep 1, 2026 371
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር አርሰናል አስቶንቪላ 1 ለ ዐ አሸንፏል። ማምሻውን በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቡካዮ ሳካ በ59ኛው ደቂቃ ግቧን አስቆጥሯል። የ24 ዓመቱ የክንፍ መስመር ተጫዋች በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ግቡን ከመረብ ላይ አሳርፏል። እምብዛም ግልጽ የግብ እድሎች ባልተፈጠሩበት ጨዋታ አርሰናል ያገኘውን የግብ እድል በሚገባ ተጠቅሟል። አስቶንቪላ ወደ አርሰናል የግብ ክልል በተደጋጋሚ ጊዜ ቢደርስም ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ ማድረግ ተስኖታል። በ75 ሚሊዮን ፓውንድ ከኒውካስትል ዩናይትድ ወደ አርሰናል የተዘዋወረው ብሩኖ ጉማራይሽ ተቀይሮ በመግባት የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የወቅቱ የሊጉ ሻምፒዮን አርሰናል ተከታታይ ድሉን አግኝቷል። በአንጻሩ በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት በርካታ ቁልፍ ተጫዋቾቹን ያጣው አስቶንቪላ ተከታታይ ሽንፈቱን አስተናግዷል። አስቶንቪላ በሁለቱ የሊግ ጨዋታዎች ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ ማድረግ አልቻለም። በሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር አስቶንቪላ ከአዲስ አዳጊው ሁል ሲቲ ጋር ይጫወታል። በለንደን ደርቢ አርሰናል ከቼልሲ የሚያደርገው ጨዋታ ከወዲሁ ተጠባቂ ነው። የሶስተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከነሐሴ 29 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳሉ።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሴካፋ ማጣሪያ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቀቀ
Aug 31, 2026 347
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በካፍ የሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ የደረጃ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የደቡብ ሱዳኑን ዬ ጆይንት ስታርስን 6 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። በኪጋሊ ፔሌ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ እፀገነት ግርማ፣ ብዙአየሁ ታደሰ፣ ማህሌት ምትኩ፣ እሙሽ ዳንኤል፣ ምህረት አየለ እና ረድኤት አስረሳኸኝ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ማውሪን ናንኪንጋ በፍጹም ቅጣት ምት የዬ ጆይንት ስታርስን የማስተዛዘኛ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በማጣሪያው ሶስተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። ንግድ ባንክ በግማሽ ፍጻሜው በዩጋንዳው ካዌምፔ ሙስሊም ሌዲስ መሸነፉን ተከትሎ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የመሳተፍ ህልሙ ማክተሙ ይታወቃል።
አርጀንቲናው ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ ከብሔራዊ ቡድኑ ራሱን አገለለ
Aug 31, 2026 183
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የ39 ዓመቱ ሊዮኔል ሜሲ ከአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ራሱን ማግለሉን ይፋ አድርጓል። ሜሲ በኢንስታግራም ገጹ ባሰፈረው መልዕክት ከፍጻሜው ጨዋታ አንስቶ ነገሮችን በጥልቀት ካሰብኩ በኋላ፣ ከብሔራዊ ቡድን ራሴን ማግለሌን ለሁሉም ማሳወቅ እፈልጋለሁ ሲል ተናግሯል። ውሳኔው ውስጤን ቢጎዳውም እና በጣም ስሜታዊ የሚያደርገኝ ቢሆንም ራሴን የማግለሉ ጊዜ አሁን ነው ብሏል። የአርጀንቲናን ማልያ ለብሼ የምችለውን ሁሉ አድርጊያሁ፣ አርጀንቲናዊ በመሆናችሁ ኩራት እንዲሰማችሁ ለማድረግም ሁሉንም ነገር ሰጥቻለሁ ብሏል። ሜሲ አያይዞም የብሔራዊ ቡድን ቆይታው ሁልጊዜ በልቡ እንደሚኖር ገልጾ፣ አሁን ላይ አዲስ እና ወጣት ተጫዋቾች ዕድሉን ማግኘት እንዳለባቸው አንስቷል። ይህንን የስንብት ጽሑፍ የጻፈው ከዓለም ዋንጫው ፍጻሜ ጨዋታ ከሁለት ቀናት በኋላ እንደነበር ገልጾ፣ ከአባቱ ሞት በኋላ እያሳለፈው ያለው ጊዜ ዛሬ ላይ ውሳኔውን እንዲያሳልፍ እንዳስገደደው አመልክቷል። በእነዚህ 20 ዓመታት ውስጥ አርጀንቲናውያን ላሳዩት ፍቅር ምስጋና ያቀረበ ሲሆን ከብሔራዊ ቡድኑ ጎን በመልካምም በክፉም ጊዜ እንደሚቆም ተናግሯል። የሜሲ ውሳኔ የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን መነጋገሪያ ሆኗል። ሊዮኔል ሜሲ ከእ.አ.አ ከ2005 እስከ 2026 በአርጀንቲና ማልያ ባደረጋቸው 207 ጨዋታዎችን 125 ጎሎችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የምንጊዜም የሀገሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኗል። በአርጀንቲና ማልያ 65 ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ አቀብሏል። በቅርቡ በተካሄደው 23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ስምንት ጎሎችን ያስቆጠረ ሲሆን በአጠቃላይ በውድድሩ ላይ 22 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ከፈረንሳዊው ኪሊያን ምባፔ (23 ጎሎች) በመቀጠል በዓለም ዋንጫው የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ደረጃ ዝርዝር ውስጥ ተቀምጧል። ሊዮኔል ሜሲ በታሪኩ በአጠቃላይ 46 ዋንጫዎችን በማንሳት በእግር ኳስ ታሪክ ከፍተኛውን የዋንጫ ብዛት የሰበሰበ ባለክረብ-ወሰን ተጫዋች ነው። ሊዮኔል ሜሲ ከአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ጋር በአጠቃላይ የተለያዩ ዋንጫዎችን አንስቷል። የፊፋ ዓለም ዋንጫ ፣ ሁለት የኮፓ አሜሪካ ዋንጫዎች፣ የአውሮፓ እና ደቡብ አሜሪካ ሻምፒዮናዎችን ያገናኘው የፋይናሊሲማ ዋንጫ፣ እንዲሁም የኦሊምፒክ የወርቅ ሜዳሊያ እና ከ20 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ክብርን ተጎናጽፏል። ሊዮኔል ሜሲ በአሁኑ ሰዓት ለአሜሪካው ኢንተር ሚያሚ ክለብ እየተጫወተ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ተጋጣሚዎቹን አውቋል
Aug 31, 2026 211
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ከ20 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የማጣሪያ ውድድር የዕጣ ማውጣት ስነ ስርዓት ዛሬ በሩዋንዳ ኪጋሊ ተካሄዷል። በሴካፋ ዞን የምትገኘው ኢትዮጵያ በምድብ አንድ ከአዘጋጇ ታንዛንያና ሩዋንዳ ጋር ተደልድላለች። ዩጋንዳ፣ ሱዳን እና ጅቡቲ በምድብ ሁለት የሚገኙ ሀገራት ናቸው። በምድብ ሶስት ደቡብ ሱዳን፣ ኬንያና ብሩንዲ ተደልድለዋል። ከ20 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ውድድር ከመስከረም 6 እስከ 20 ቀን 2019 ዓ.ም ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ አንደኛና ሁለተኛ የሚወጡ ሀገራት እ.አ.አ በ2027 በጋና በሚካሄደው ከ20 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ዞኑን ወክለው ይሳተፋሉ። በስድስት አህጉራዊ ዞኖች በሚካሄዱት የማጣሪያ ውድድሮች በእያንዳንዱ ቀጣና ሁለት ሀገራት ለአፍሪካ ዋንጫው ያልፋሉ።
አስቶንቪላ ከአርሰናል ፡- የሳምንቱ ተጠባቂ የሊግ ፍልሚያ
Aug 31, 2026 167
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ዛሬ ምሽት አራት ሰዓት ላይ አስቶንቪላ ከአርሰናል በቪላ ፓርክ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የሁለተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። አስቶንቪላ በመጀመሪያ የሊግ ጨዋታው በብራይተን የ4 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ሻምፒዮኑ አርሰናል የዋንጫ ክብሩን የማስጠበቅ ጉዞውን ኮቨንተሪ ሲቲን 3 ለ 0 በመርታት ጀምሯል። አስቶንቪላ በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት ቁልፍ ተጫዋቾቹን ማጣቱ ስብስቡ ላይ መሳሳት ፈጥሯል። ሞርጋን ሮጀርስ፣ ኦሊ ዋትኪንዝ፣ ኤሚሊያኖ ማርቲኔዝ፣ ኤዝሪ ኮንሳ፣ ዩሪ ቲሊማንስ፣ ሉካስ ዲኝ እና ዶኒየል ማለን አስቶንቪላን የለቀቁ ተጫዋቾች ናቸው። ኒኮላስ ጃክሰን፣ ሊኦን ጎሬትዝካ፣ አሮን ዋን-ቢሳካ፣ ማቴዎ ሩጌሪ አሌሃንድሮ ጋርናቾ (ውሰት ማንችስተር ዩናይትድ) ጨምሮ የተለያዩ ተጫዋቾችን በማስፈረም አቅሙን ለማጠናከር እየሰራ ነው። አርሰናል በበኩሉ ብሩኖ ጉማሬሽ፣ ክሪስቶስ ዞሊስ፣ ኤዝሪ ኮንሳ፣ ፒዬሮ ሂንካፒዬ እና ኢላን ሜስሊየርን በማስፈረም ስብስቡን አጠናክሯል። ክሪስቶስ ዞሊስ በመጀመሪያው የሊጉ ጨዋታ መልካም እንቅስቃሴ አድርጓል። ሁለቱ ክለቦች ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 54 የሊግ ጨዋታዎች መካከል አርሰናል 29ኙን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። አስቶንቪላ 11 ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ 14 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። አርሰናል በ54ቱ ጨዋታዎች ላይ 92 ግቦችን ሲያስቆጥር አስቶንቪላ በበኩሉ 48 ጎሎችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ባለፉት አምስት የሊግ ግንኙነታቸው አርሰናል በሶስቱ ሲያሸንፍ አስቶንቪላ አንድ ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። ክለቦቹ ባለፈው የውድድር ዓመት ባደረጓቸው ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አርሰናል ሁለቱንም አሸንፏል። ከዝውውር እንስቃሴዎችና ከወቅታዊ ብቃት አንጻር አርሰናል የማሸነፍ የቅድሚያ ግምቱን አግኝቷል። ተጋጣሚው አስቶንቪላ ከመጀመሪያ የሊግ ሽንፈቱ በኋላ በሜዳው የሚያደርገው ጨዋታ ጠንካራ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችለው መልካም አጋጣሚ ነው። የ39 ዓመቱ አውስትራሊያዊ ጃሬድ ጊሌት ተጠባቂውን ጨዋታ በመሐል ዳኝነት እንዲመሩ ተመድበዋል።
ማንችስተር ዩናይትድ በብሩኖ ፈርናንዴዝ ሀትሪክ ታግዞ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን አስመዘገበ
Aug 30, 2026 280
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ ኤፕስዊች ታውንን 5 ለ 2 ረትቷል። ማምሻውን በኦልትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብሩኖ ፈርናንዴዝ ሶስት ግቦችን (አንድ በፍጹም ቅጣት ምት) በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። የ31 ዓመቱ አማካይ በአዲሱ የውድድር ዓመት ሀትሪክ የሰራ የመጀመሪያ ተጫዋች ሆኗል። ብሪያን ምቡሞ እና የኤፕስዊቹ ጃኮብ ግሪቭስ በራሱ ላይ ቀሪዎቹን ጎሎች ለማንችስተር ዩናይትድ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሀትሪክ የሰራው ፈርናንዴዝ ለሙቤሞ ጎል ኳስ አመቻችቶ አቀብሏል።የጨዋታው ኮከብ በመባልም ተመርጧል። ሌፍ ዴቪስ እና ቹባ አክፖም የኤፕስዊችን ጎሎች ከመረብ ጋር አገናኝተዋል። በመጀመሪያው አጋማሽ ብልጫ ተወስዶበት የነበረው ማንችስተር ዩናይትድ በሁለተኛው አጋማሽ ፍጹም የበላይነት ወስዶ ተጫውቷል። ውጤቱን ተከትሎ ዩናይትድ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን አግኝቷል። አዲስ አዳጊው ኤፕስዊች ታውን በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በሶስተኛ ሳምንት መርሐ ግብር ማንችስተር ዩናይትድ ከኤቨርተን፣ ኤፕስዊች ታውን ከሊቨርፑል ጋር ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።