ቀጥታ፡
ስፖርት
ማንችስተር ሲቲ ነጥብ ጣለ
Jan 1, 2026 43
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 23/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ19ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሰንደርላንድ እና ማንችስተር ሲቲ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ማምሻውን በስታዲየም ኦፍ ላይት በተካሄደው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድሎችን በመፍጠር የተሻለ የነበረ ቢሆንም ሊጠቀምባቸው አልቻለም። ሰንደርላንድ በተደራጀ መከላከል እና የመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴ ተጋጣሚውን ፈትኗል።   ውጤቱን ተከትሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ማንችስተር ሲቲ ነጥቡን ወደ 41 ከፍ አድርጓል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ያለው የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ከፍ ብሏል። ሰንደርላንድ በበኩሉ በ29 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ተቀምጧል። ማምሻውን በተመሳሳይ ሰዓት በተደገ ሌላኛው ጨዋታ ብሬንትፎርድ እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ ያለ ግብ አቻ ወጥተዋል። ዛሬ አስቀድመው በተካሄዱ ጨዋታዎች ሊቨርፑል ከሊድስ ዩናይትድ ያለ ግብ አቻ ሲለያዩ የክሪስታል ፓላስ እና ፉልሃም ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። ዛሬ በፈረንጆች 2026 አዲስ ዓመት የተደረጉት አራቱም የሊጉ ጨዋታዎች በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል። ጨዋታዎቹም የግብ ድርቀት አጋጥሟቸዋል።
የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር የምድቡ መሪ ሆና ጨርሳለች 
Jan 1, 2026 84
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ስድስት የመጨረሻ ጨዋታዎች ትናንት ማምሻውን ተደርገዋል። በማራካሽ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኮትዲቯር ቦትስዋናን 3 ለ 2 አሸንፋለች። ለኮትዲቯር ጂን-ፍሊፕ ክራሶ፣ ኢቫን ጉሳንድ እና ባዙማና ቱሬ የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጉሎር ካንጋ እና ዴኒስ ቡዋንጋ ለቦትስዋና ግቦቹን አስቆጥረዋል። አስቀድማ ወደ ጥሎ ማለፍ የገባችው የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ ባለቤት ኮትዲቯር በሰባት ነጥብ ምድቡን በመሪነት አጠናቃለች። ቦትስዋና በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በተያያዘም በአጋዲር ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ካሜሮን ሞዛምቢክን 2 ለ 1 አሸንፋለች።   ክርስቲያን ኮፋን እና የሞዛምቢኩ ኔኔ በራሱ ግብ ላይ የማሸነፊያ ግቦችን አስቆጥረዋል። ጌኒ ካታሞ ለሞዛምቢክ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። አስቀድሞ ጥሎ ማለፍ የገባችው ካሜሮን በሰባት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጣ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በምድቡ ሶስት ነጥብ በማግኘት ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችው ሞዛምቢክ ምርጥ ሶስተኛ በመሆን ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ጨዋታዎች ተጠናቀዋል። የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ከታህሳስ 25 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳል።
የአፍሪካ እግር ኳስ ፈር ቀዳጇ ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ዋንጫ 
Jan 1, 2026 177
ክፍል አንድ እንደ መነሻ እ.አ.አ የካቲት 8 ቀን 1957 በአፍሪካ እግር ኳስ ውስጥ ታሪካዊ ከሚባሉ ቀናት ውስጥ አንዱ ነው። በካርቱም ግራንድ ሆቴል ሱዳን፣ኢትዮጵያ፣ግብጽና ደቡብ አፍሪካ የአፍሪካን እግር ኳስ በበላይነት የሚመራውን ተቋም ለመመስረት ምክክር ላይ ናቸው። አህጉሪቷን የሚወክለው ኮንፌዴሬሽን ለማቋቋም መነሻ የሆነው ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር(ፊፋ) እ.አ.አ በ1956 በፖርቹጋል ሊዝበን ባካሄደው ዓመታዊ ኮንግረስ ላይ የአፍሪካ አገራት ተወካዮች ከሌሎች አህጉራዊ የእግር ኳስ ማህበራት ጋር ያደረጓቸው መደበኛ ምክክሮች ናቸው።   በካርቱም የተሰበሰቡት አራት አገራት የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን በይፋ መሰረቱ። ግብጻዊውን አብደል አዚዝ አብደላ ሳሌምን በሙሉ ድምጽ የካፍ የመጀመሪያው ፕሬዝዳንት አድርገው መረጡ። ካፍን ያቋቋሙት አገራት እ.አ.አ በ1957 የአፍሪካ ዋንጫ በሱዳን እንዲካሄድ ወሰኑ። የመጀመሪያውን የካፍ መተዳደሪያና የውድድር ደንቦች ያዘጋጁት አቶ ይድነቃቸው ተሰማ ናቸው። የኢትዮጵያ የመጀመሪያ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎና የፎርፌ ውጤት የመጀመሪያው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ ከየካቲት 10 እስከ 16 1957 በሱዳን ካርቱም ተካሄዷል። በውድድሩ ላይ ሱዳን፣ኢትዮጵያና ግብጽ ተሳታፊ ነበሩ። በፈረንጆቹ አዲስ ዓመት ማንችስተር ሲቲ ከሰንደርላንድ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው አስቀድሞ በአፍሪካ ዋንጫ ላይ ትሳተፋለች ተብሎ የነበረው ደቡብ አፍሪካ ከአገሪቷ በነበረው የአፓርታይድ የዘር መድሎ ምክንያት ከውድድሩ ውጪ ሆናለች። ደቡብ አፍሪካ ከውድድሩ ውጪ የሆነቸው በአፓርታይድ ሕግ ነጮች ሙሉ በሙሉ በነጭ ወይም በሙሉ የተገነባ ብሔራዊ ቡድን እንጂ መቀላቀል አንችልም በማለታቸው ምክንያት ነው። በዚህም ምክንያት ከደቡብ አፍሪካ ጋራ በግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዋን ልታደርግ የነበረችው ኢትዮጵያ 2 ለ 0 በፎርፌ በማሸነፍ ለፍጻሜው አልፋለች። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ግብጽ ሱዳንን 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜ አለፈች። እ.አ.አ የካቲት 16 1957 በካርቱም ዓለም አቀፍ ስታዲየም በተደረገው የፍጻሜ ጨዋታ ግብጽ ኢትዮጵያን 4 ለ 0 በማሸነፍ ታሪካዊውን የአፍሪካ ዋንጫ አነሳች። አራቱንም ግቦች ያስቆጠረው የፊት መስመር ተጫዋቹ መሐመድ ዲያብ አል-አታር ሲሆን በአፍሪካ ዋንጫ ፍጻሜ አራት ግቦችን ያስቆጠረ የመጀመሪያው ተጫዋችና በአምስት ግቦች የመጀመሪያው የውድድሩ ኮከብ ግቢ አግቢ በመሆን ድርብ ታሪክ ጽፏል።   ኢትዮጵያ በመጀመሪያው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎዋ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቀቀች። በመጀመሪያው የአፍሪካ ዋንጫ በውድድሩ ላይ ለመሳተፍ ምንም የማጣሪያ ውድድር አልተደረገም። በመጀመሪያ የአፍሪካ ዋንጫ የተሳተፉት የኢትዮጵያ ተጫዋቾች ግብ ጠባቂ ሚካኤል ጊላ ተከላካዮች አየለ ተሰማ፣መኩሪያ ከበደ አስፋው፣አዳሙ ዓለሙ፣አዳል ተክለስላሴ አማካዮች ናስር በርሄና ሳሙኤል ዘውዴ አጥቂዎች አብርሃም ባይሩ፣አምደስላሴ ነጸረ፣አስፋው ብርሃኔና ከበደ መታፈሪያ ናቸው። በአፍሪካ ዋንጫና እግር ኳስ ፈር ቀዳጅ ከሆኑ አገራት መካከል አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎዋን በሱዳን አሀዱ ብላ ጀመረች። የኢትዮጵያ ሁለተኛ ተሳትፎ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1959 በግብጽ በተካሄደው ሁለተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ አድርጋለች። ሱዳን ሌላዋ በውድድሩ ላይ የተሳተፈች አገር ናት። የውድድሩ ፎርማት በአገራቱ መካከል እርስ በእርስ በሚደረጉ ጨዋታዎች የተሻለ ውጤት ያስመዘገበው ቡድን የአፍሪካ ዋንጫ የሚያነሳበት ነበር። በዚሁ መሰረት ኢትዮጵያ በውድድሩ ባደረገቻቸው ጨዋታዎች በግብጽ 4 ለ 0፤ በሱዳን 1 ለ 0 ተሸንፋለች። በፍጻሜው ግብጽ ሱዳንን 2 ለ 1 በማሸነፍ ለሁለተኛ ተከታታይ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አንስታለች። ኢትዮጵያ ብቸኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ያነሳችበት ታሪካዊ አጋጣሚ   ሶስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ የተካሄደው በኢትዮጵያ አዘጋጅነት እ.አ.አ በ1962 ነው። የአፍሪካ ዋንጫ ውድድሩ ቀደም ብለው ከተካሄዱት ሁለት የአፍሪካ ዋንጫዎች ለየት የሚያደርገው አራት አገራት ለመጀመሪያ ጊዜ የተሳተፉበት ነው። ኢትዮጵያ የውድድሩ አዘጋጅ በመሆኗ ሀገራችን በቀጥታ ለውድድሩ ስታልፍ ፤ በተመሳሳይ የግብፅ ቡድንም የ1959 የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ዋንጫ አሸናፊ ቡድን ስለነበር በቀጥታ ለ3ኛ የአፍሪካ ዋንጫ ሲያልፉ ዩጋንዳና ቱኒዚያ የማጣሪያ ጨዋታ አድርገው ለአፍሪካ ዋንጫ አልፈዋል። በሶስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ የነበሩት አቶ ይድነቃቸው ተሰማ ሲሆኑ ውድድሩን ያስተናገደው ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ስታዲየም(የአሁኑ አዲስ አበባ ስታዲየም) ነበር። ኢትዮጵያ በግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዋ ቱኒዚያን 4 ለ 2 አሸንፋለች። አጥቂው ሉቺያኖ ቫሳሎ በ32ኛው በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠራት ግብ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ያስቆጠረችው የመጀመሪያ ግቧ ሆኖ ተመዝግቧል። ቫሳሎ በ75ኛው ደቂቃ በጨዋታ ግብ አስቆጥሯል። አጥቂው መንግስቱ ወርቁ እና ግርማ ተክሌ ቀሪዎችን ግቦች ለኢትዮጵያ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ግብጽ ዩጋንዳን 2 ለ 1 በማሸነፍ ለፍጻሜው ከኢትዮጵያ ጋር ደረሰች። በፍጻሜው ጨዋታ አሊ መሐመድ ባዳዊ አብደል ፋታህ በ35ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት በግብ ግብጽን መሪ ማድረግ ችላ ነበር። ከእረፍት መልስ ግርማ ተክሌ በ74ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ኢትዮጵያን አቻ አድርጋለች። በ75ኛው ደቂቃ አሊ መሐመድ ባዳዊ አብደል ፋታህ በድጋሚ ግብጽን መሪ ያደረገች ግብ አስቆጠረ። አጥቂው መንግስቱ ወርቁ በ84ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ኢትዮጵያን በድጋሚ አቻ አደረገ። ጨዋታው በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሁለት አቻ በሆነ ውጤት በመጠናቀቁ ጨዋታው ወደ ጭማሬ ሰዓት አምርቷል። በጭማሬ 30 ደቂቃው ኢታሎ ቫሳሎ በ101ኛው እና መንግስቱ ወርቁ በ118ኛው ደቂቃ ባስቆጠራቸው ግቦች ኢትዮጵያ 4 ለ 2 በማሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ አህጉራዊውን ዋንጫ ከፍ አድርጋለች። በፍጻሜው ጨዋታ ሁለት ግቦች ያስቆጠረው አጥቂው መንግስቱ ወርቁ በአጠቃላይ በውድድሩ ላይ ሶስት ጎሎችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ ጨርሷል። ለመጀመሪያ ጊዜ ስድስት አገራት የተሳተፉበት የአፍሪካ ዋንጫ የኢትዮጵያ ቀጣዩ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ እ.አ.አ በ1963 በጋና አስተናጋጅነት በተካሄደው አራተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው። በውድድሩ ለመጀመሪያ ጊዜ ስድስት ብሔራዊ ቡድኖች የተሳተፉ ሲሆን በሁለት ምድብ እያንዳንዳቸው ሶስት አገራት ተደልድለው ጨዋታቸውን አድርገዋል። የውድድሩ ፎርማት በየምድቡ አንደኛ ሆኖ የጨረሰ አገር ወደ ፍጻሜው እንዲሁም ሁለተኛ የወጡ አገራት ለደረጃው ያለፉበት ነበር። ኢትዮጵያ በምድብ አንድ ከአዘጋጅ አገር ጋና ቱኒዚያ ጋር ተደልድላች። በአክራ ስፖርት ስታዲየም ኢትዮጵያ ከጋና ጋር ባደረገችው ጨዋታ 2 ለ 0 ተሸንፋለች። በሁለተኛ ጨዋታዋ ኢትዮጵያ አጥቂው መንግስቱ ወርቁ ሁለት እንዲሁም ግርማ ተክሌና ግርማ ተስፋዬ ባስቆጠሯቸው አንድ አንድ ግቦች ቱኒዚያን 4 ለ 2 አሸንፋለች። ኢትዮጵያ ከምድቡ ሁለተኛ ሆና በማጠናቀቋ ለደረጃ ጨዋታ የቀረበች ሲሆን በግብጽ 3 ለ 0 ተሸንፋለች። በፍጻሜው ጋና ሱዳንን 3 ለ 0 በማሸነፍ ዋንጫውን አነሳች። ኢትዮጵያ ለአምስተኛ ተከታታይ ጊዜ የተሳተፈችበት የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1965 በቱኒዚያ አስተናጋጅነት በተካሄደው አምስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለተከታታይ አምስተኛ ጊዜ ተሳትፋለች። በውድድሩ ላይ ስድስት አገራት ተሳትፈዋል። ኢትዮጵያ በምድብ አንድ ከቱኒዚያና ሴኔጋል ጋር ተደልድላለች። በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታዋ በቱኒዚያ 4 ለ 0 ተሸንፋለች። ኢትዮጵያ በሁለተኛው የምድብ ጨዋታዋ በሴኔጋል 5 ለ 1 ተሸንፋለች። በጨዋታው ለኢትዮጵያ ብቸኛዋን ግብ ያስቆጠረው ሉቺያኖ ቫሳሎ በፍጹም ቅጣት ምት ነበር። በፍጻሜው ጋና ቱኒዚያን 3 ለ 2 በማሸነፍ ለሁለተኛ ተከታታይ ጊዜ የአፍሪካን ዋንጫ ማንሳት ችላለች። ኢትዮጵያ ለሁለተኛ ጊዜ ያዘጋጀችው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ 1968 የተካሄደውን ስድስተኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ያዘጋጀችው ኢትዮጵያ ነበረች። ውድድሩን ያስተናገደው ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ስታዲየም(የአሁኑ አዲስ አበባ ስታዲየም) ነበር። በሻምፒዮናው ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ስምንት አገራት ተሳትፈዋል። ኢትዮጵያ በምድብ አንድ ከኮትዲቭዋር፣አልጄሪያና ዩጋንዳ ጋር የተደለደለች ሲሆን ሶስቱንም የምድብ ጨዋታዎቿን አሸንፋለች። በመጀመሪያ ጨዋታዋ ኢትዮጵያ ግርማ አስመሮም ተስፋይ በጨዋታና ሉቺያኖ ቫሳሎ በፍጹም ቅጣት ምት ባስቆጠሯቸው ግቦች ዩጋንዳን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ኢትዮጵያ በሁለተኛ ጨዋታዋ በኩረጽዮን ገብረሕይወት ባስቆጠራት ግብ ኮትዲቭዋርን 1 ለ 0 ረታለች። በምድቡ የመጨረሻ ጨዋታ ኢትዮጵያ አጥቂው መንግስቱ ወርቁና ሸዋንግዛው አጎናፍር በጨዋታ እንዲሁም ሉቺያኖ ቫሳሎ በፍጹም ቅጣት ምት ባስቆጠሯቸው ግቦች አልጄሪያን 3 ለ 1 በማሸነፍ ከምድቧ አንደኛ በመውጣት ለግማሽ ፍጻሜው አልፋለች። ኢትዮጵያ በግማሽ ፍጻሜው ጨዋታዋን ያደረገችው ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ጋር ነበር። ራውል አልበርት ኪዱሙ ማንታንቱ በሶስተኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን መሪ አድርጎል። ሊኦን ሙንጋሙኒ በ16ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ የኮንጎን መሪነት ወደ 2 ለ 0 ከፍ አድርጓል። ሉቺያኖ ቫሳሎ በ25ኛው ደቂያ ያስቆጠራት ግብ ኢትዮጵያን ወደ ጨዋታው እንድትመለስ አድርጓል። መንግስቱ ወርቁ በ65ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ኢትዮጵያን አቻ አድርጓል። መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት መጠናቀቁ ጨዋታው ወደ ጭማሪ 30 ደቂቃ አመራ። በጭማሬ ሰዓቱ ሊኦን ሙንጋሙኒ በ100ኛው ደቂቃ ያስቆጠራትን ግብ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን አሸናፊ በማድረግ ወደ ፍጻሜው እንድታልፍ አድርጎታል። ኢትዮጵያ ለደረጃው ባደረገችው ጨዋታ ላውረን ፖኩ ባስቆጠራት ግብ 1 ለ 0 ተሸንፋ ለሁለተኛ ጊዜ ባዘጋጀችው ውድድር አራተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ኢትዮጵያ ከፍተኛ ግብ ያስተገደችበት ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሱዳን እ.አ.አ 1970 ሱዳን ባዘጋጀችው ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ ለሰባተኛ ጊዜ በአህጉራዊው የውድድር መድረክ ተሳትፋለች። በውድድሩ ላይ ስምንት አገራት ተሳትፈዋል። ኢትዮጵያ በምድብ አንድ ከኮትዲቭዋር፣ካሜሮንና ሱዳን ጋር ተደልድላለች። ኢትዮጵያ በምድብ የመጀመሪያ ጨዋታዋ በሱዳን 3 ለ 0 በሆነ ውጤት ተረታለች። በሁለተኛው ጨዋታም በካሜሮን 3 ለ 2 የተሸነፈች ሲሆን መንግስቱ ወርቁ ለኢትዮጵያ ሁለቱንም ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፏል። በመጨረሻው የምድብ ጨዋታ ኢትዮጵያ በኮትዲቭዋር 6 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት ተሸንፋለች። መንግስቱ ወርቁ ለኢትዮጵያ ብቸኛዋን ግብ ከመረብ ላይ ያሳረፈ ተጫዋች ነበር። በዚህ ጨዋታ አጥቂው ላውረን ፖኩ አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። ውጤቶቹን ተከትሎ ኢትዮጵያ በምድቡ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ ይዛ ያጠናቀቀች ሲሆን በውድድሩ 12 ግቦችን ተቆጥረውባታል። በፍጻሜው ሱዳን ጋናን 1 ለ 0 በማሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አንስታለች። ኢትዮጵያ ከስድስት ዓመታት ቆይታ በኋላ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ስምንተኛ ተሳትፎዋን ለማድረግ ስድስት ዓመት መጠበቅ ነበረባት። እ.አ.አ በ1976 ራሷ ለሶስተኛ ጊዜ ባዘጋጀችው የአፍሪካ ዋንጫ በድጋሚ ወደ ውድድር ተሳትፎ ተመልሳለች። በውድድሩ ላይ አሁንም የተሳተፉ አገራት ቁጥር ስምንት ነበር። ኢትዮጵያ በውድድሩ በምድብ አንድ ከግብጽ፣ዩጋንዳና ጊኒ ጋር ተደልድላለች። በመጀመሪያው የምድብ ጨዋታ ኢትዮጵያ በሰለሞን ሽፈራውና ተስፋዬ ስዩም ግቦች ዩጋንዳን 2 ለ 0 አሸንፋለች። በሁለተኛ ጨዋታዋ ኢትዮጵያን በጊኒ የ2 ለ 1 ሽንፈት አጋጥሟታል። ሰለሞን ሽፈራው ኢትዮጵያን ከሽንፈት ያልታደገችውን ብቸኛ ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በመጨረሻ የምድብ ጨዋታዋ ኢትዮጵያ ከግብጽ ጋር አንድ አቻ ተለያይታለች። መሐመድ አሊ ለኢትዮጵያ ግቧን ያስቆጠረ ተጫዋች ነው። ውጤቶቹን ተከትሎ ኢትዮጵያ በአራት ነጥብ ከምድቧ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቋ ወደ ግማሽ ፍጻሜው ማለፍ ሳትችል ቀርታለች። በፍጻሜው ሞሮኮ ጊኒን በማሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን ማንሳት ቻለች። ይቀጥላል ….
በፈረንጆቹ አዲስ ዓመት ማንችስተር ሲቲ ከሰንደርላንድ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 1, 2026 102
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ19ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ምሽት አምስት ሰዓት ላይ ሰንደርላንድ ከማንችስተር ሲቲ በስታዲየም ኦፍ ላይት የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። ሰንደርላንድ በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ በ40 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት ወደ ሊጉ ያደገው ሰንደርላንድ ጥሩ ጊዜ እያሳለፈ ይገኛል። በጥሩ አቋም የሚገኘው ማንችስተር ሲቲ ወጥነት ያለው ብቃት በሊጉ ላይ እያሳየ ይገኛል። ውኃ ሰማያዊዎቹ ካሸነፉ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያላቸውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ ያደርጋሉ። ባለሜዳው ሰንደርላንድ ማሸነፍ ከሁለት ተከታታይ የአቻ ውጤቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት መመለስ ያስችለዋል።   በሌሎች መርሐ ግብሮች ሊቨርፑል ከሊድስ ዩናይትድ እና ክሪስታል ፓላስ ከፉልሃም በተመሳሳይ ምሽት 2 ከ 30 ላይ ይጫወታሉ።   ብሬንትፎርድ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ ከምሽቱ አምስት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
አልጄሪያ የምድቧ መሪ ሆና አጠናቀቀች
Dec 31, 2025 111
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አምስት የመጨረሻ ጨዋታዎች ተካሄደዋል። በሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አልጄሪያ ኢኳቶሪያል ጊኒን 3 ለ 1 አሸንፋለች። ዚነዲን ቤላይድ፣ ፋሬስ ቻይቢ እና ኢብራሂም ማዛ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኢሚሊዮ ንሱዌ ሎፔዝ ለኢኳቶሪያ ጊኒ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። አስቀድሞ ጥሎ ማለፍ የገባችው አልጄሪያ በዘጠኝ ነጥብ የምድቡ መሪ ሆና አጠናቃለች። አልጄሪያ ከናይጄሪያ በመቀጠል የምድብ ጨዋታዎቿን ያሸነፈች ሁለተኛ ሀገር ሆናለች። በአንጻሩ በምድቡ ሶስተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ኢኳቶሪያል ጊኒ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃን በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች።   በተያያዘም ማምሻውን በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው የምድቡ ጨዋታ ቡርኪናፋሶ ሱዳንን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ላሲና ትራኦሬ እና አርሴኔ ኩዋሲ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሱዳን በ24ኛው ደቂቃ ያገኘችውን ፍጹም ቅጣት ምት አል ጎዞሊ ኖህ ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቷን ያረጋገጠችው ቡርኪናፋሶ በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ሱዳን በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ ምርጥ ሶስተኛ ሆና ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድል ቀንቶታል 
Dec 31, 2025 76
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ኢትዮጵያ መድንን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ናትናኤል ዳንኤል እና አዲስ ግደይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ረመዳን የሱፍ ለኢትዮጵያ መድን ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ ቢኒያም ካሳሁን በ73ኛው ደቂቃ ላይ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በሊጉ ሶስተኛ ድሉን ያሳካው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ15 ነጥብ ደረጃውን ከ14ኛ ወደ 11ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ13 ነጥብ ከነበረበት 13ኛ ደረጃ ወደ 14ኛ ዝቅ ብሏል። ዛሬ በተደረገ ሌላኛው ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና መቻልን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ከታህሳስ 25 ቀን 2015 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳል።
በአፍሪካ ዋንጫ ለበርካታ ጊዜ የተሰለፉ ተጫዋቾች
Dec 31, 2025 156
የአፍሪካ ዋንጫ የአፍሪካ እግር ኳስ ቁንጮ መድረክ ነው። ሀገራት በየሁለት ዓመቱ በአንድ መድረክ ተገናኝተው ዋንጫውን ለማንሳት ይፋለማሉ። ግቦች፣ ዋንጫዎች፣ ኮከብ ተጫዋቾች እና ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪዎች የዜና አርዕስት ሆነው ጎልተው ይታያሉ። በአህጉራዊ መድረክ ብቃታቸው ሳይዋዥቅ ለረጅም ጊዜያት የተሰለፉ ተጫዋቾች የአፍሪካ እግር ኳስ ምልክቶች ናቸው።   ካሜሮናዊው ተከላካይ ሪጎበርት ሶንግ 36 ጨዋታዎችን በማድረግ በርካታ ጨዋታዎች ላይ ከተሰለፉ ተጫዋቾች መካከል ይጠቀሳል። በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል ሶንግ በስምንት የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ በመሳተፍ አይበገሬነቱን አሳይቷል። በተጫዋችነት ዘመኑ ሁለት የአፍሪካ ዋንጫን አንስቷል። የብሄራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ ሆኖም አገልግሏል።   እንደ ሶንግ በተመሳሳይ 36 ጨዋታዎችን ያደረገው ጋናዊው አንድሬ አየው ነው። በአፍሪካ እግር ኳስ ውስጥ ስሙ ጎልቶ ከሚነሳው አብዲ ፔሌ ልጆች መካከል አንዱ የሆነው አንድሬ አየው በስምንት የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎን አድርጓል። ቡድኑ በሁለት አጋጣሚ የፍጻሜ ተፈላሚ እንዲሆን ማድረግ ችሏል። ጋና በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አለመሳተፏን ተከትሎ አየው የበርካታ ጊዜ የመሰለፍ ክብረ ወሰን የመስበር እድል አምልጦታል።   ግብጻዊው አህመድ ሀሰን በስምንት የአፍሪካ ዋንጫ 32 ጨዋታዎችን በማድረግ ሌላኛው ተጫዋች ነው። ሀሰን አራት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን በማንሳት በስኬት ያሸበረቀ ታሪክ አለው።   ማሊያዊው ሰይዱ ኬይታ፣ ካሜሮናዊው ጀረሚ ንጂታፕ እና ጋናዊው አሳሞሃ ጊያን በተመሳሳይ 31 ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫው ተሰልፈው ለሀገራቸው ተጫውተዋል። የኮትዲቯሩ ያያ ቱሬ፣ የናይጄሪያው ጆሴፍ ዮቦ፣ የካሜሮኑ ሳሙኤል ኤቶ እና የቱኒዚያው የሱፍ ምሳክኒ በተመሳሳይ 29 ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫው ተሰልፈዋል። ኮትዲቭዋርያኑ ማክስ-አለን ግራዴል እና ቡባካር ባሪ እንዲሁም ግብጻዊው ግብ ጠባቂ ኢሳም ኤል ሃዳሪ በተመሳሳይ 28 ጊዜ ጨዋታቸውን አድርገዋል። የኮትዲቭዋሮቹ ሲያካ ቲዬኔ እና ኮሎ ሃቢብ ቱሬ በተመሳሳይ በ27 ጨዋታዎች ላይ ተሰልፈው ተጫውተዋል። የተጫዋቾቹ ለበርካታ ጊዜ መሰለፍ በአህጉራዊው መድረክ ለረጅም ጊዜ የመቆየት አቅም፣ አልሸነፍ ባይነት እና በጫና ውስጥ የማለፍ ብርታትን የሚያመላከት ነው።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል 
Dec 31, 2025 101
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 22/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ ሳምንት በመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከኢትዮጵያ መድን ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። የ2016 ዓ.ም የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ካደረጋቸው 11 ጨዋታዎች መካከል ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በሶስቱ ተሸንፏል። በስድስት ጨዋታዎች ላይ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ 13 ግቦችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ 13 ጎሎችን አስተናግዷል። ንግድ ባንክ በ12 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ መድን በውድድር ዓመቱ 11 ጨዋታዎችን አከናውኖ በሶስቱ ድል ሲቀናው አራት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 10 ጎሎች ተቆጥረውበታል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ13 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ትኩረትን ስቧል። በሌላኛው መርሃ ግብር መቻል ከኢትዮጵያ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። መቻል እስከ አሁን በሊጉ 11 ጨዋታዎችን ያደረገ ሲሆን አራት ጨዋታዎችን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በስድስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ11ዱ ጨዋታዎች ላይ 16 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 10 ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ20 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ ካከናወናቸው 11 ጨዋታዎች መካከል ሶስት ጊዜ ድል ሲቀናው በአምስቱ ተሸንፏል። ሶስት ጊዜ ነጥብ ጥሏል። ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር 11 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ኢትዮጵያ ቡና በ12 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ጨዋታው መቻል ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ኢትዮጵያ ቡና ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ሶስት ነጥብ ለማግኘት የሚያደርጉት ነው።
በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ
Dec 31, 2025 108
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ መርሃ ግብር ዛሬ በሚደረጉ ጨዋታዎች ይጠናቀቃል። በምድብ አምስት ሱዳን ከቡርኪናፋሶ በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም የሚያከናውኑት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።   በምድቡ ተመሳሳይ ሶስት ነጥብ ያላቸው ቡርኪናፋሶ እና ሱዳን በግብ ክፍያ ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ሁለቱም ሀገራት ጥሎ ማለፍ መግባታቸውን አረጋግጠዋል። በዚሁ ምድብ በተመሳሳይ ምሽት አንድ ሰዓት ኢኳቶሪያል ጊኒ ከአልጄሪያ በሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።   በምድቡ ኢኳቶሪያል ጊኒ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃን ይዛለች። ተጋጣሚዋ አልጄሪያ በስድስት ነጥብ ጥሎ ማለፉን መቀላቀሏ ይታወቃል። ኢኳቶሪያል ጊኒ ከምድቡ መውደቋ ይታወቃል። አልጄሪያ ካሸነፈች የምድቡ መሪ ሆና ታጠናቅቃለች። በምድብ ስድስት ጋቦን ከኮትዲቯር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በማራካሽ ስታዲየም ይጫወታሉ።   በምድቡ ሁለት ጊዜ ሽንፈት ያስተናገደችው ጋቦን ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻው አራተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር በአራት ነጥብ ምድቡን እየመራች ነው። ጋቦን ከውድድሩ መሰናበቷ ይታወቃል።በአንጻሩ ኮትዲቯር ጥሎ ማለፉን መቀላቀሏን አረጋግጣለች። በዚሁ ምድብ ሞዛምቢክ ከካሜሮን በተመሳሳይ ምሽት አራት ሰዓት ላይ በአጋዲር ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።   ሞዛምቢክ በሶስት ነጥብ ሶስተኛ፣ ካሜሮን በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ሞዛምቢክ ምርጥ ጥሎ ማለፍ የገባች ሌላኛዋ ሀገር ናት።ተጋጣሚዋ ካሜሮን የመጨረሻ 16ቱን ተቀላቅላለች። የምድብ ጨዋታዎች ዛሬ ከተጠናቀቁ በኋላ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ከታህሳስ 25 እስከ ታህሳስ 28 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ይካሄዳሉ።
በተጠባቂው ጨዋታ አርሰናል አስቶንቪላን በማሸነፍ የሊጉን መሪነት አጠናከረ 
Dec 30, 2025 168
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 21/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 19ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርሰናል አስቶንቪላን 4 ለ 1 ረቷል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጋብርኤል ማጋሌስ፣ ማርቲን ዙቢሜንዲ፣ሊያንድሮ ትሮሳርድ እና ጋብርኤል ጄሱስ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኦሊ ዋትኪንስ በ30ኛ ዓመት የልደት ቀኑ ብቸኛውን ጎል ለአስቶንቪላ ከመረብ ላይ አሳርፏል። አርሰናል በተለይም በሁለተኛው አጋማሽ የወሰደው ብልጫ ጨዋታውን እንዲያሸንፍ አስችሎታል። በውድድር ዓመቱ 14ኛ ድሉን ያስመዘገበው የሊጉ መሪ አርሰናል ነጥቡን ወደ 45 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ ማድረግ ችሏል። ከስምንት የሊግ ተከታታይ ድሎች በኋላ ሽንፈት ያስተናገደው አስቶንቪላ በ39 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል።   በሌላኛው መርሃ ግብር ማንችስተር ዩናይትድ እና ዎልቭስ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ጆሹዋ ዚርክዜ ለዩናይትድ፣ ላዲስላቭ ክሬጅቺ ለዎልቭስ ግቦቹን አስቆጥረዋል።   ቼልሲ እና ቦርንማውዝ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ኤንዞ ፈርናንዴዝ በጨዋታ እና ኮል ፓልመር በፍጹም ቅጣት ምት ለቼልሲ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዴቪድ ብሩክስ እና ጀስቲን ክላይቨርት ለቦርንማውዝ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሌሎች ጨዋታዎች ኒውካስትል ዩናይትድ በርንሌይን 3 ለ 1፣ ኤቨርተን ኖቲንግሃም ፎረስትን 2 ለ ዐ አሸንፈዋል። ዌስትሃም ዩናይትድ እና ብራይተን ያደረጉት ጨዋታ ሁለት አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል።
ሴኔጋል እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅለዋል 
Dec 30, 2025 97
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 21/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አራት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ማምሻውን ተደርገዋል። በታንጀር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሴኔጋል ቤኒንን 3ለ 0 አሸንፋለች። አብዱላዬ ሴክ እና ሃቢቡ ሞሃመዱ ዲያሎ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የሴኔጋሉ ተከላካይ ካሊዱ ኩሊባሊ በ71ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ውጤቱን ተከትሎ ሴኔጋል በሰባት ነጥብ ከምድቧ አንደኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ቤኒን በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።   በሌላኛው የምድቡ ጨዋታ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ቦትስዋናን 3 ለ 0 አሸንፋለች። በአል መዲና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጋኤል ካኩታ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ናትናኤል ምቡኩ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በሰባት ነጥብ በሴኔጋል በግብ ክፍያ ተበልጣ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። ቦትስዋና ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች።
ቱኒዚያ ወደ ጥሎ ማለፍ ገብታለች 
Dec 30, 2025 109
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 21/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ማምሻውን ተካሄደዋል። በራባት ኦሊምፒክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ታንዛንያ እና ቱኒዚያ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ፌይሰል ሳሉም ለታንዛንያ በጨዋታ፣ እስማኤል ጋርቢ በፍጹም ቅጣት ምት ለቱኒዚያ ግቦቹን አስቆጥረዋል።   ውጤቱን ተከትሎ ቱኒዚያ በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ታንዛንያ በሁለት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀች ሲሆን ምርጥ ሶስተኛ ሆና ለማለፍ የሌሎች ምድቦችን ውጤት ትጠብቃለች። በዚሁ ምድብ ዛሬ ማምሻውን በፌዝ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ናይጄሪያ ዩጋንዳን 3 ለ 1 አሸንፋለች።   ራፋኤል ኦንዬዲካ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ፖል ኦኑቹ ቀሪዋን ጎል ለናይጄሪያ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሮጀርስ ማቶ ለዩጋንዳ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። የዩጋንዳው ጀማል ሳሊም በ57ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል።   ውጤቱን ተከትሎ አስቀድሞ ጥሎ ማለፍ የገባችው ናይጄሪያ በዘጠኝ ነጥብ ምድቡን በመሪነት አጠናቅቃለች። በአፍሪካ ዋንጫው የምድብ ጨዋታዎችን በሙሉ ያሸነፈች የመጀመሪያዋ ሀገር ሆናለች። የምስራቅ አፍሪካዋ ዩጋንዳ በአንድ ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዛ ከውድድሩ ተሰናብታለች።
የአፍሪካ ዋንጫ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪዎች
Dec 30, 2025 94
የአፍሪካ ዋንጫ በርካታ ክዋክብቶች ደምቀው የታዩበት መድረክ ነው። በሀገራት መካከል ያለው ተቀናቃኝነት፣ አይረሴ ገጠመኞች፣ በደጋፊዎች የተሞሉ ስታዲየሞች እና ሀገራቸውን ለክብር ያበቁ እና ታሪክ የጻፉ ተጫዋቾች በአፍሪካ ዋንጫው ላይ ታይተዋል። የአፍሪካ ዋንጫ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪዎችም የአህጉሪቷ የእግር ኳስ ታሪክ አካል ነው። ካሜሮናዊው ኮከብ ሳሙኤል ኢቶ 18 ጎሎችን በውድድር ላይ በማስቆጠር የቀዳሚነት ስፍራን ይዟል። ኢቶ 10 ጎሎቹን ያስቆጠረው በስድስት የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ ነው። እ.አ.አ በ2006 እና 2008 በተካሄዱ ውድድሮች ላይ ኮከብ ግብ አስቆጣሪ ሆኖ አጠናቋል። ሁለት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን ከሜሮን ጋር አንስቷል።   ኮትዲቯራዊው ላውረን ፖኩ 14 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ተጫዋቹ ግቦቹን ያስቆጠረው በሁለት የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ ነው። ፖኩ እ.አ.አ በ1970 በሱዳን አስተናጋጅነት በተካሄደው ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ ላይ አምስት ግቦችን በማስቆጠር በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ በአንድ ጨዋታ በርካታ ጎሎችን ከመረብ ላይ ያሳረፈ ተጫዋች ክብረ ወሰንን ባለቤት ነው። ናይጄሪያው ራሺድ ያኪኒ በ20 የአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታዎች ላይ 13 ግቦችን በማስቆጠር ቀጣዩ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ያኪኒ እ.አ. በ1994 የተካሄደውን የአፍሪካ ዋንጫ ያነሳ ሲሆን የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪም ነበር።   ግብጻዊው ሀሰን ኤል-ሻዝሊ በስምንት ጨዋታዎች 12 ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ይህም በአንድ ጨዋታ በአማካይ 1 ነጥብ 50 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል እንደ ማለት ነው። ይህም በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ ውጤታማው አጥቂዎች ከሚባሉት ተርታ እንዲሰለፍ አድርጎታል። ኤል-ሻዝሊ በሁለት የአፍሪካ ዋንጫዎች ፍጻሜ ላይ ሀትሪክ የሰራ ብቸኛው ተጫዋች ነው። ካሜሮናዊው ፓትሪክ ምቦማ፣ ግብጻዊው ሆሳም ሀሰን እና ኮትዲቭራዊው ዲዲየር ድሮግባ በተመሳሳይ 11 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ ተከታዩን ደረጃ ይዘዋል’ ፓትሪክ ምቦማ በአፍሪካ ዋንጫ ባደረጋቸው 17 ጨዋታዎች 11 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል።   ሆሳም ሀሰን እና ዲዲየር ድሮግባ በአፍሪካ ዋንጫ 21 ጨዋታዎችን አድርገው በተመሳሳይ 11 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። በውድድሩ ላይ ትኩረት ከሚስቡት ጉዳዮች አንዱ ማን ኮከብ ግብ አግቢ ሆኖ ያጠናቀቃል? የሚለው ጉዳይ ነው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም