ቀጥታ፡
ስፖርት
የአፍሪካ ዋንጫ እና ሽልማቱ
Dec 25, 2025 78
የአፍሪካ ዋንጫ ሽልማት ለአህጉሪቷ እግር ኳስ ልማት ያለው መልካም አንድምታ፡- የአፍሪካ ዋንጫ የአህጉሪቷ ግዙፍ የስፖርት መድረክ ነው። የአፍሪካ ዋንጫ በተሳታፊ ሀገራት ብዛት፣ በፉክክር እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው እይታ እያደገ ይገኛል። ይህም ውድድሩን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ተመልካቾች እንዲያዩት እና ውድድሩን ስፖንሰር የማድረግ ፍላጎት እንዲያድግ ምክንያት ሆኗል። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። በውድድሩ 24 ሀገራት እየተሳተፉ ይገኛል።   የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ለውድድሩ ተሳታፊ ሀገራት በርካታ ገንዘብ ለመሸለም ተዘጋጅቷል። ዋንጫ የሚያነሳው ሀገር የ10 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ያገኛል። የአሸናፊ ሽልማት እ.አ.አ በኮትዲቭዋር ከተካሄደው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሰባት ሚሊዮን ዶላር ሽልማት የ43 በመቶ ብልጫ አለው። ሁለተኛ የሚወጣው አገር የ4 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ይበረከትለታል። በግማሽ ፍጻሜው የወደቁ ሁለት አገራት እያንዳንዳቸው 2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዶላር፤ በሩብ ፍጻሜው የተሰናበቱ አራት አገራት እያንዳንዳቸው 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ዶላር ያገኛሉ። በጥሎ ማለፉ ለሚሰናበቱ ስምንት ሀገራት እያንዳንዳቸው የ800 ሺህ ዶላር ሽልማት ይሰጣቸዋል። በምድባቸው ምርጥ ሶስተኛ ሆነው የሚያጠናቅቁ ሁለት ሀገራት በተመሳሳይ 700 ሺህ፣ በየምድባቸው አራተኛ ደረጃን ይዘው የሚያጠናቅቁ ስድስት ሀገራት እያንዳንዳቸው የ500 ሺህ ዶላር ሽልማት ይበረከትላቸዋል። 24ቱም ተሳታፊ ሀገራት በውድድሩ ላይ እንደሚያስመዘግቡት ውጤት የሽልማቱ ተቋዳሽ ይሆናሉ። የአፍሪካ ዋንጫን የሚያሸንፈው ሀገር በአጠቃላይ 11 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ሊያገኝ ይችላል።   የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ዘንድሮ ያዘጋጀው ሽልማት እ.አ.አ በ2021 በካሜሮን አስተናጋጅነት ከተካሄደው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጋር ሲነጻጸር የ40 በመቶ ብልጫ አለው። የካፍ ፕሬዝዳንት ፓትሪስ ሞትሴፔ (ዶ/ር) በአፍሪካ ዋንጫ እና በሌሎች የአፍሪካ ውድድሮች ላይ የታየው የሽልማት መጠን ማደግ በአህጉሪቷ እግር ኳስ የፋይናንስ እድገት የሚያሳይ እና የአፍሪካን የእግር ኳስ ምህዳር እንደሚደግፍ አመልክተዋል። ሽልማቱ ለአፍሪካ እግር ኳስ ልማት፣ የእግር ኳስ ፌዴሬሽኖች እና የእግር ኳስ ባለድርሻ አካላትን የሚደግፍ ነው ብለዋል። የአፍሪካ ዋንጫ ሽልማት በአህጉራት ደረጃ በሚካሄዱ ውድድሮች ላይ በሽልማት መጠኑ በሶስተኛ ደረጃ ላይ ይቀመጣል። የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር (ዪኤፋ) ለአውሮፓ ዋንጫ የ360 ሚሊዮን ዶላር አጠቃላይ ሽልማት የሚያዘጋጅ ሲሆን አሸናፊው ሀገር 30 ሚሊዮን ዶላር ያገኛል። ኮፓ አሜሪካ (ደቡብ አሜሪካ) አጠቃላይ ሽልማት 72 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ነው። አሸናፊው ሀገር 16 ሚሊዮን ዶላር ይወስዳል። የአፍሪካ ዋንጫ ሽልማት ከእስያ ዋንጫ እና የሰሜንና መካከለኛው አሜሪካ (ኮንካካፍ) ይበልጣል።   እስያ ዋንጫ አጠቃላይ ሽልማቱ 15 ሚሊዮን ዶላር ሲሆን ውድድሩን የሚያሸንፈው ሀገር አምስት ሚሊዮን ዶላር ያገኛል። ኮንካካፍ አጠቃላይ ሽልማት 15 ሚሊዮን የአሜሪካን ሚሊዮን ዶላር ነው። ዋንጫውን የሚያነሳው ሀገር የአምስት ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ይበረከትለታል። የአፍሪካ ዋንጫ የገንዘብ ሽልማት እድገት ከአህጉሪቷ አልፎ ዓለም አቀፍ ትኩረትን የሳበ ጉዳይ ሆኗል። የገንዘብ ሽልማቱ ከጥቅም ባለፈ ለሀገራት የኢኮኖሚ ጠቃሜታዎችን የሚያስገኝ ነው። ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው የአፍሪካ ዋንጫ ሽልማት ለአፍሪካ እግር ኳስ ልማት ስትራቴጂካዊ የኢኮኖሚ ማዕቀፍ ነው።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ 
Dec 25, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 16/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይከናወናሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየም ከቀኑ 7 ሰዓት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከምድረገነት ሽሬ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 10 ጨዋታዎች በአራቱ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ቡድኑ በ17 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ምድረገነት ሽሬ ከ10 የሊጉ ጨዋታዎች መካከል ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። አምስት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። ምድረገነት ሽሬ በ14 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱም ክለቦች በሊጉ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ ባደረጋቸው 10 ጨዋታዎች አምስቱን ሲያሸንፍ በአራቱ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። ቡድኑ በ16 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ እስከ አሁን ማሸነፍ የቻላቸው ጨዋታዎች ብዛት ሁለት ብቻ ናቸው። ሶስት ጊዜ ሲሸነፍ በአምስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። የ2016 ዓ.ም የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ11 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። ሸገር ከተማ ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው 10 ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አራት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 10 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ያሸነፈው ሃዋሳ ከተማ ሶስት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። ሁለት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ሃዋሳ ከተማ በ17 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ቡና ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ ቡና በ12 ነጥብ 14ኛ፣ ድሬዳዋ ከተማ በ13 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዘዋል። ጨዋታዎቹ በዋንጫ ፉክክሩ ግምት የሚሰጣቸው ናቸው።
አልጄሪያ አፍሪካ ዋንጫን በድል ጀምራለች
Dec 24, 2025 100
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 15/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አምስት ሁለተኛ ጨዋታ አልጄሪያ ሱዳንን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሪያድ ማህሬዝ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኢብራሂም ማዛ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የአፍሪካ ዋንጫ እውነታዎች በአፍሪካ ዋንጫ ልንመለከታቸው የሚገቡ አምስት ተጫዋቾች የሱዳኑ ሳላህ አዲል በ39ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ውጤቱን ተከትሎ አልጄሪያ ምድብ አምስትን በሶስት ነጥብ መምራት ጀምራለች። በትውልድ አልጄሪያዊ በዜግነት ፈረንሳዊ የቀድሞ ተጫዋች ከልጁ ሉካ ጋር በመሆን ጨዋታውን በስታዲየም በመገኘት ተከታትሏል። የአልጄሪያው ሪያድ ማህሬዝ በሁለተኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል የዘንድሮው ውድድር ፈጣን ጎል ሆኗል። የ34 ዓመቱ ተጫዋች በአፍሪካ ዋንጫው ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ ሰባት ከፍ አድርጓል። በአጠቃላይ ለአልጄሪያ ያስቆጠራቸው ግቦች ብዛት 36 ደርሰዋል። በምድብ አምስት ዛሬ በተደረገ ጨዋታ ቡርኪናፋሶ ኢኳቶሪያል ጊኒን 2 ለ 1 አሸንፋለች። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ቡርኪናፋሶ ኢኳቶሪያል ጊኒን አሸነፈች 
Dec 24, 2025 87
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 15/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አምስት የመጀመሪያ ጨዋታ ቡርኪናፋሶ ኢኳቶሪያል ጊኒን 2 ለ 1 አሸንፋለች። በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማርቪን አኒቦህ በ85ኛው ደቂቃ በግንባሩ በመግጨት ያስቆጠረው ግብ ኢኳቶሪያል ጊኒን መሪ አድርጓል። ጆርጅ ሚኑጉ በ95ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ቡርኪናፋሶ አቻ ሆናለች። ጨዋታው በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ ሲባል 98ኛው ደቂቃ ላይ ኤድመንድ ታፕሶባ ባስቆጠረው ግብ ቡርኪናፋሶ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝታለች። የቡርኪናፋሶው አጥቂ ላሲና ትራኦሬ በ71ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ከጨዋታ ውጪ በመሆኑ ተሽሯል። የኢኳቶሪያል ጊኒው ተከላካይ ባሲሊዮ ንዶንግ በ50ኘው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ንዶንግ በአፍሪካ ዋንጫው ቀይ ካርድ የተመለከተ የመጀመሪያ ተጫዋች ሆኗል።   ውጤቱን ተከትሎ ቡርኪናፋሶ ምድብ አምስትን በሶስት ነጥብ መምራት ጀምራለች። በዚሁ ምድብ አልጄሪያ ከሱዳን ምሽት 12 ሰዓት ላይ በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የአፍሪካ ዋንጫ እውነታዎች
Dec 24, 2025 176
የአፍሪካ ዋንጫ ከተጀመረ ወደ ሰባት አስርት ዓመታት ገደማ አስቆጥሯል። አህጉራዊው የእግር ኳስ መድረክ የተጀመረው እ.አ.አ በ1957 ነው። የአፍሪካ ዋንጫን ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ ያሉ እውነታዎችን እንመልከት የመጀመሪያው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ በ1957 ሲጀመር ተሳታፊ ሀገራቱ ሶስት ብቻ ነበሩ። እነሱም አዘጋጇ ሱዳን፣ ኢትዮጵያ እና ግብጽ ናቸው። ግብጽ በፍጻሜው ጨዋታ ኢትዮጵያን 4 ለ 0 በማሸነፍ ታሪካዊውን ዋንጫ አንስታለች። ሶስቱ ሀገራት የአፍሪካ ዋንጫ መስራች ሀገራት በመሆን ሁሌም በታሪክ ይወሳሉ። ከእ.አ.አ 2019 የአፍሪካ ዋንጫ አንስቶ 24 ሀገራት እየተሳተፉ ይገኛል።   በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ የመጀመሪያውን ግብ ያስቆጠረው ግብጻዊው ራፋት አቲያ ነው። አቲያ ግቧን ያስቆጠረው ግብጽ ሱዳንን 2 ለ 1 ባሸነፈችበት የመጀመሪያው የአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታ ላይ ነው። ኢትዮጵያ ከመጀመሪያው የአፍሪካ ዋንጫ አንስቶ እስከ አሁን ለ11 ጊዜ ተሳትፋለች። ኢትዮጵያ በውድድሩ ላይ ለመጨረሻ ጊዜ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ2021 ካሜሮን ባዘጋጀችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1962 ያዘጋጀችውን ሶስተኛውን የአፍሪካ ዋንጫ በማንሳት ብቸኛ ድሏን አስመዘግባለች። በፍጻሜው ጨዋታ ግብጽን 4 ለ 2 በመርታት ዋንጫውን ከፍ አድርጋለች። የፍጻሜውን ጨምሮ ሁለት ግቦችን ያስቆጠረው አጥቂው መንግስቱ ወርቁ የአፍሪካ ዋንጫ ኮከብ ተጫዋች ሆኖ ተመርጧል። በወቅቱ የኢትዮጵያ አጥቂ የነበረው ሉቺያኖ ቫሳሎ እና የግብጹ ባደዊ አብደል ፋታህ በተመሳሳይ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆነው አጠናቀዋል። ኢትዮጵያ ሶስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን ያስተናገደች ሲሆን ለመጨረሻ ጊዜ ውድድሩን ያዘጋጀችው እ.አ.አ በ1976 የተካሄደውን 10ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ነው። በፍጻሜው ሞሮኮ ጊኒን በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች።   ግብጽ የአፍሪካ ዋንጫን በማንሳት ስኬታማዋ ሀገር ናት። በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ ግብ ያስቆጠረ በእድሜ ትልቁ ተጫዋች የግብጹ ሆሳም ሀሰን ነው። ግብጽ እ.አ.አ በ2006 ባዘጋጀችው 25ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን 4 ለ 1 ስታሸነፍ ሆሳም ሀሰን በ39 ዓመት እድሜ ጎል ማስቆጠር ችሏል። ሆሳም ሀሰን በአሁኑ ሰዓት የግብጽ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ነው። በአፍሪካ ዋንጫ በእድሜ ትንሹ ግብ አስቆጣሪ የጋቦኑ ሺቫ ንዚጉ ነው። ጋና እና ናይጄሪያ እ.አ.አ በ2000 በጣምራ ባዘጋጁት 22ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ሀገሩ በደቡብ አፍሪካ 3 ለ 1 ስትሸነፍ ብቸኛውን ግብ በ16 ዓመቱ ከመረብ ላይ ማሳረፍ ችሏል። በአፍሪካ ዋንጫ የተሰለፈ በእድሜ ትንሹ ተጫዋችም ነው። የአፍሪካ ዋንጫ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ካሜሮናዊው ሳሙኤል ኢቶ ሲሆን 18 ግቦችን ከመረብ አሳርፏል። በአፍሪካ ዋንጫው ለበርካታ ጊዜ የተሰለፉ ተጫዋቾች ካሜሮናዊው ሪጎበርር ሶንግ እና ጋናዊው አንድሬ ዴዴ አየው ሲሆኑ በተመሳሳይ 36 ጨዋታዎችን አድርገዋል። የአፍሪካ ዋንጫ ካዘጋጁ ሀገራት መካከል ዘጠኙ ዋንጫውን በሀገራቸው አስቀርተዋል። ይህ የአዘጋጅነት ጥቅም የሚያስገውን ውጤት ያሳያል።   በመጀመሪያዋ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎዋ ዋንጫ ያነሳችው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ናት። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1968 ባዘጋጀችው ስድስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ (በቀድሞ ስሟ ዛየር) በፍጻሜው ጋናን 1 ለ 0 በማሸነፍ ለፍጻሜ ደርሳለች። የአፍሪካ ዋንጫን ፈጣኗን ግብ ያስቆጠረው ግብጻዊው ሀሰን ኤል ሻዝሊ ነው። ጋና እ.አ.አ በ1963 ባዘጋጀችው አራተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሻዝሊ ዛምቢያ ላይ በ23ኛው ሴኮንድ ግብ ያስቆጠረ ሲሆን ክብረ ወሰኑ እስከ አሁን አልተሰበረም። የግብጹ ግብ ጠባቂ ኢሳም ኤል ሃዳሪ እ.አ.አ በ2017 በተካሄደው 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በ44 ዓመቱ በመሰለፍ በእድሜ አንጋፋው ተጫዋች ሆኗል። በአፍሪካ ዋንጫው 17 ተጫዋቾች ሀትሪክ ሰርተዋል። ግብጻዊው መሐመድ ዲያብ አል-ታር በመጀመሪያው የአፍሪካ ዋንጫ ሀገሩ በፍጻሜው ኢትዮጵያን ስታሸንፍ የመጀመሪያውን ሀትሪክ ሰርቷል። ግብጻውያኑ አህመድ ሀሰን እና ኢሳም ኤል ሃዳሪ በተመሳሳይ አራት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን በማንሳት ለበርካታ ጊዜ ዋንጫውን ያነሱ ተጫዋቾች ናቸው። የግብጹ ሀሰን ሺሃታ እና የጋናው ቻርልስ ግያምፊ በተመሳሳይ ሶስት ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ ስኬታማ አሰልጣኞች ናቸው።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል 
Dec 24, 2025 87
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ባህር ዳር ከተማ ከፋሲል ከነማ ይጫወታሉ። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው 10 ጨዋታዎች መካከል ሶስቱን ሲያሸንፍ በተመሳሳይ በሶስቱ ተሸንፏል። አራት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ቡድኑ በ13 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ በሊጉ እስከ አሁን 10 ጨዋታዎች በአምስቱ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ አምስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በ20 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ፋሲል ከነማ በሊጉ እስከ አሁን በሊጉ ሽንፈት ያላስተናገደ ብቸኛው ቡድን ነው። የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፈ የሊጉን መሪነት በጊዜያዊነት ከሲዳማ ቡና ይረከባል። በሌላኛው መርሃ ግብር አርባምንጭ ከተማ ከመቀሌ 70 እንደርታ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ ምንም ጨዋታ ማሸነፍ አልቻለም። በአምስቱ ሲሸነፍ አምስት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። ቡድኑ በ20 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ በሊጉ እስከ አሁን ሶስት ነጥብ አላገኘም። በአምስቱ ጨዋታዎች ሲሸነፍ አምስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። ቡድኑ በተመሳሳይ አምስት ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ 19ኛ ደረጃን በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሁለቱ ቡድኖች በሊጉ የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይፋለማሉ። ነጌሌ አርሲ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ነጌሌ አርሲ በ13 ነጥብ ደረጃን ይዟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በስምንት ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ሀድያ ሆሳዕና ከወላይታ ድቻ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሀድያ ሆሳዕና በ10 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ወላይታ ድቻ በተመሳሳይ 10 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት እስከ ታህሳስ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ሲዳማ ቡና ሊጉን በ21 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው።
የአፍሪካ ዋንጫ መስራች ሀገር ሱዳን ከአልጄሪያ ጋር ትጫወታለች  
Dec 24, 2025 65
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ አራተኛ ቀኑን ይዟል። በዕለቱ የምድብ አምስት እና ስድስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በምድብ አምስት የምስራቅ አፍሪካዋ ሱዳን ከአልጀሪያ ጋር ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ትጫወታለች። ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። የአፍሪካ ዋንጫ መስራች ሀገር ከሆኑት መካከል አንዷ የሆነችው ሱዳን በውድድሩ ላይ ስትሳተፍ የአሁኑ ለ10ኛ ጊዜ ነው። እ.አ.አ በ1970 ራሷ ያዘጋጀችውን ሰባተኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ጋናን በማሸነፍ አንስታለች። ሱዳን እ.አ.አ በ1957 ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ያዘጋጀች ታሪካዊ ሀገር ናት። ተጋጣሚዋ አልጄሪያ በአፍሪካ ዋንጫው ለ19ኛ ጊዜ ተሳትፎዋን ታደርጋለች። የሰሜን አፍሪካዊቷ ሀገር የ17ኛው እና የ32ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድሮች አሸናፊ ናት። በዚሁ ምድብ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ቡርኪናፋሶ ከኢኮቶሪያል ጊኒ በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካው ዋንጫ ከዚህ ቀደም አንድ ጊዜ ተገናኝተዋል። ኢኮቶሪያል ጊኒ እ.አ.አ በ2015 ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ቡርኪናፋሶ በአፍሪካ ዋንጫው ለ14ኛ ጊዜ እንዲሁም ኢኳቶሪያል ጊኒ ለአምስተኛ ጊዜ ተሳትፏቸውን የሚያደርጉ ይሆናል። ሁለቱም ሀገራት የአፍሪካ ዋንጫን አንስተው አያውቁም። በተያያዘም የምድብ ስድስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ኮትዲቭዋር ከሞዛምቢክ በማራካሽ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሀገራቱ በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። እ.አ.አ በ1986 በግብጽ በተካሄደው 15ኛው የአፍሪካ በምድብ ተገናኝተው ኮትዲቭዋር 3 ለ 0 አሸንፋለች። ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ1996 ባዘጋጀችው 20ኛው የአፍሪካ ዋንጫም በምድብ አራት ተጫውተው ኮትዲቭዋር 1 ለ 0 ማሸነፏ የሚታወስ ነው። በአፍሪካ ዋንጫው ለ25ኛ ጊዜ የምትሳተፈው ኮትዲቭዋር ሶስት ጊዜ ዋንጫ አንስታለች። በአንጻሩ ለስድስተኛ ጊዜ የምትሳተፈው ሞዛምቢክ ከዚህ ቀደም በነበራት ተሳትፎ ከምድቧ አልፋ አታውቅም። በዚሁ ምድብ ካሜሮን ከጋቦን ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በአጋዲር ስታዲየም ይጫወታሉ። ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ዋንጫ ለአምስት ጊዜ ተገናኝተው ጋቦን አንድ ጊዜ ስታሸንፍ በቀሪ አራት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ካሜሮን በአፍሪካ ዋንጫው ለ22ኛ ጊዜ የምትሳተፍ ሲሆን አምስት ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት ስኬታማ ሀገር ናት። በውድድሩ ላይ ዘጠነኛ ተሳትፎዋን የምታደርገው ጋቦን በበኩሏ ትልቁ ውጤቷ በ20ኛው እና 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ የደረሰችባቸው ናቸው። ካሜሮን በአፍሪካ ዋንጫው ለመጀመሪያ ጊዜ ጋቦንን ለማሸነፍ ትጫወታለች።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ተስተካካይ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሸገር ከተማን አሸነፈ
Dec 23, 2025 84
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 14/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የአንደኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሸገር ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ትዕግስት አዳነ እና ንግስት በቀለ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ገነሜ ወርቁ ለሸገር ከተማ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ29 ነጥብ ደረጀውን ከአምስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሸገር ከተማ በ27 ነጥብ ከነበረበት አራተኛ ደረጃ ወደ አምስተኛ ዝቅ ብሏል። የቡድኖቹ ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ በነበረው ተሳትፎ ምክንያት የተራዘመ ነው። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቀሪ ተስተካካይ መርሃ ግብሩን ታህሳስ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ከሲዳማ ቡና ጋር እንደሚያደርግ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ዙር ከተስተካካይ መርሃ ግብሮች ውጪ መጠናቀቁ ይታወቃል።
በአፍሪካ ዋንጫ ትኩረት የሳቡ ወጣት ተጫዋቾች
Dec 23, 2025 142
የአፍሪካ ዋንጫ ኮከብ እና አንጋፋ ተጫዋቾች የሚታዩበት መድረክ ብቻ አይደለም። እምቅ ችሎታ እና ብሩህ ተስፋ ያላቸው ወጣት ተጫዎቾች ራሳቸውን የሚያስተዋውቁበትም ጭምር ነው። በተለያዩ የአፍሪካ ዋንጫዎች ደምቀው የታዩ የአፍሪካ ወጣት ተጫዋቾችን ለመመልከት ተችሏል። ጋናዊው አቢዲ ፔሌ፣ የናይጄሪያው ንዋንኮ ካኑ፣ ካሜሮናዊው ሳሙኤል ኤቶ፣ የግብጹ ሆሳም ሚዶ፣ የዛምቢያው ካሉሻ ቡዋሊ፣ ኮትዲቯራዊው ዲዲየር ድሮግባ እና የጋቦኑ ፒዬር-ኤሜሪክ ኦቦሚያንግ በወጣትነት እድሜያቸው በአፍሪካ ዋንጫው ተሳትፎ በማድረግ በቀሪ እግር ኳስ ህይወታቸው ስኬታማ ከሆኑ ተጫዋቾች መካከል ይጠቀሳሉ። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። በአፍሪካ ዋንጫው ጎልተው ይታያሉ የተባሉ ተጫዋቾችን እንመልከት። ቢላል ኤል ካኑስ (ሞሮኮ) ኤል ካኑስ በአውሮፓ ከሚጫወቱ የአፍሪካ ተስፈኛ ተጫዋቾች መካከል አንዱ ነው። በአሁኑ ሰዓት ከሌይስተር ሲቲ በውሰት ወደ ስቱትጋርት አቅንቶ እየተጫወተ ይገኛል።   በቤልጂየም የተወለደው የ21 ዓመቱ ተጫዋች ለአውሮፓዊቷ ሀገር በታዳጊ ብሄራዊ ቡድኖች በመሰለፍ ከእ.አ.አ 2022 አንስቶ ለሞሮኮ ዋና ቡድን እየተጫወተ ይገኛል። የአጥቂ አማካይ ተጫዋቹ እ.አ.አ በ2022 በኳታር በተካሄደው 22ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ሞሮኮ ከክሮሺያ ጋር ባደረገችው የደረጃ ጨዋታ ላይ የመጀመሪያ ጨዋታውን ለሀገሩ አድርጓል። ከዛ ጊዜ አንስቶ ለሞሮኮ 26 ጨዋታዎችን አድርጎ ሁለት ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በውስን ቦታዎች እና በጠባብ ክፍቶች መሐል ያለው የፈጠራ አቅም ተጫዋቹ አድናቆት እንዲቸረው አድርጓል። ላሚን ካማራ (ሴኔጋል)   የ21 ላሚን ካማራ የሴኔጋልን ማልያ ለመጀመሪያ ጊዜ የለበሰው እ.አ.አ በ2022 በአልጄሪያ አስተናጋጅነት በተካሄደው ሰባተኛው የአፍሪካ ሀገራት እግር ኳስ ሻምፒዮና (ቻን) ላይ ነው። የሀገር ውስጥ ሊግ ተጫዋቾች ብቻ በሚጫወቱበት ውድድር ከሀገሩ ዋንጫ አንስቷል። በወቅቱ በሩብ ፍጻሜው ሞሪታኒያ ላይ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠራት ጎል ቡድኑ ለግማሽ ፍጻሜ እንዲያልፍ አስችሎታል። ከዛ ወቅት አንስቶ ለሴኔጋል 34 ጨዋታዎች አድርጎ ስድስት ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። እ.አ.አ በ2024 ከሜትዝ ወደ ሞናኮ በማቅናት እየተጫወተ የሚገኝ ሲሆን በ38 ጨዋታዎች ሁለት ጎሎችን አስቆጥሯል። ለሴኔጋል ዋናው ቡድን በመደበኛነት እየተሰለፈ የሚገኘው ካማራ ከአማካይ ክፍል በመነሳት ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል የሚያደርጋቸው ፈጣን ሩጫዎች እና የሚፈጥራቸው የግብ እድሎች አድናቆት እንዲቸረው አድርጓል። ካርሎስ ባሌባ (ካሜሮን)   ካርሎስ ባሌባ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ለብራይተን ኤንድ ሆቭ አልቢየን የሚጫወት ነው። ተጫዋቹ በአማካይ እና በተከላካይ አማካይ ስፍራ መጫወት የሚችል ነው። በካሜሮን ዱዋላ የተወለደው ባሌባ አባቱ ለደቡብ አፍሪካ እና ካሜሮን ክለቦች ተጫውቶ አሳልፏል። እ.አ.አ በ2023 ከፈረንሳዩ ሊል ወደ ብራይተን በማምራት ድንቅ ጊዜን እያሳለፈ ይገኛል። ባሌባ ለካሜሮን የመጀመሪያ ጨዋታውን ያደረገው እ.አ.አ በ2024 ሀገሩ ከኬፕቨርዴ ጋር ባደረገችው የዓለም ማጣሪያ ጨዋታ ላይ ነው። ከዛ ጊዜ ጀምሮ ለብሄራዊ ቡድኑ 11 ጨዋታዎችን ያደረገ ሲሆን ምንም ጎል አላስቆጠረም። ታታሪነት፣ ኳስ በብቃት ማንከባለል እና ኳስን ማቀበል የተጫዋቹ መገለጫዎች ናቸው። በሜዳው ውስጥ ከሳጥን እስከ ሳጥን በሚያደርገው እንቅስቃሴ ከፖል ፓግባ፣ ቲያጎ አልካንታራ እና ኬቨን ደ ብሮይን ጋር የሚያነጻጽሩትም አሉ። ኦማር ዲያኪቴ (ኮትዲቭዋር)   የአጥቂ መስመር ተሰላፊው ኦማር ዲያኪቴ በአፍሪካ ዋንጫው ከሚጠበቁ ወጣት ተጫዋቾች መካከል አንዱ ነው። የ21 ዓመቱ ተጫዋች በአሁኑ ከፈረንሳዩ ሬሚስ በውሰት ወደ ቤልጂየሙ ሴርክል ብሩዥ በማምራት እየተጫወተ ይገኛል። ዲያኪቴ ለሀገሩ ለመጀመሪያ ጊዜ ጨዋታውን ያደረገው እ.አ.አ በ2023 ኮትዲቭዋር ከሌሴቶ ጋር ባደረገችው ጨዋታ ላይ ሲሆን ለብሄራዊ ቡድኑ ባደረጋቸው 23 ጨዋታዎች ስድስት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ በ2023 በኮትዲቭዋር አስተጋጅነት በተካሄደው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫም ተሳትፎ አድርጓል። የዲያኪቴ የአጨራረስ ብቃት እና የቦታ አያያዙ ለተከላካዮች ፈተና ነው። ትራቪስ ሙታባያ (ዩጋንዳ)   የ20 ዓመቱ ሙታባያ በምስራቅ አፍሪካ እግር ኳስ ተስፋ ከተጣለባቸው ባለ ክህሎት ተጫዋቾች መካከል አንዱ ነው። የአማካይ መስመር ተሰላፊው ከፈረንሳዩ ቦርዶ እ.አ.አ በ2025 ወደ ቱኒዚያው ስፋክሲያን በማምራት እየተጫወተ ይገኛል። በዩጋንዳ ታዳጊ ብሄራዊ ቡድኖች ላይ ድንቅ ብቃቱን ካሳየ በኋላ ከአራት ዓመት በፊት በ16 ዓመቱ በዋናው ቡድን እንዲጫወት ጥሪ ቀርቦለታል። የመጀመሪያ ጨዋታውንም ዩጋንዳ ከታንዛንያ ባደረገችው የወዳጅነት ጨዋታ ላይ አከናውኗል። ለሀገሩ እስከ አሁን ባደረጋቸው 24 ጨዋታዎችን ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ተሳትፎውን የሚያደርገው የ20 ዓመቱ ተጫዋች የመፍጠር አቅሙ፣ የስራ ታታሪነት እና ኳስ የማንከባለል ክህሎቱ አድናቆት እንዲቸረው አድርጓል። የታንዛንያው ኬልቪን ጆን፣ የዛምቢያ ሚጉዌል ቻዋ፣ የሴኔጋሉ ኢብራሂም ምባዬ፣ የሴኔጋሉ ፓፔ ማታር ሳር እና የሞሮኮው ኤሊስ ቤን ሴግሂር ሌሎች አይን ያረፈባቸው ወጣት ተጫዋቾች ናቸው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም