ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
አዳማ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ነጥብ ተጋርተዋል
Apr 30, 2025 36
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አዳማ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳዋ ሆጤሳ በ42ኛውደቂቃ ባስቆጠራት ጎል ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን መሪ ማድረግ ችሎ ነበር። መሪነቱ የዘለቀው ለሶስት ደቂቃዎች ነው። በ45ኛው ደቂቃ ነቢል ኑሪ አዳማ ከተማን አቻ አድርጓል። ከእረፍት መልስ ግብ ሳይቆጠር ጨዋታው በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ውጤቱን ተከትሎ አዳማ ከተማ በ22 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ12 ነጥብ የመጨረሻውን 18ኛ ደረጃን ይዟል። ቀን ላይ በተደረገ የ27ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ስሑል ሽሬ እና ወላይታ ድቻ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
ስሑል ሽሬ እና ወላይታ ድቻ አቻ ተለያዩ
Apr 30, 2025 42
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት የመክፈቻ ጨዋታ ስሑል ሽሬ እና ወላይታ ድቻ አንድ አቻ ተለያይተዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብርሃኑ አዳሙ በ65ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ ስሑል ሽሬ መምራት ችሎ ነበር። ብዙም ሳይቆይ በ69ኛው ደቂቃ ፀጋዬ ብርሃኑ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ወላይታ ድቻን የአንድ ነጥብ ባለቤት አድርጋለች። ውጤቱን ተከትሎ ስሑል ሽሬ በ19 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ወላይታ ድቻ በ38 ነጥብ ደረጃውን ከ6ኛ ወደ 5ኛ ከፍ አድርጓል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኙት አዳማ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ይጫወታሉ።
በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የግማሽ ፍጻሜ የባርሴሎና እና ኢንተር ሚላን ፍልሚያ
Apr 30, 2025 78
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፡- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሁለተኛ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ባርሴሎና እና ኢንተር ሚላን ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 4 ሰዓት ላይ በካምፕኑ ስታዲየም ይካሄዳል። በሩብ ፍጻሜው ባርሴሎና ቦሩሲያ ዶርትሙንድን፣ ኢንተር ሚላን ባየር ሙኒክን በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜው ደርሰዋል። ሁለቱ ክለቦች በውድድሩ በግማሽ ፍጻሜ ደረጃ ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። እ.አ.አ 2009/10 ኢንተር ሚላን በደርሶ መልስ ውጤት 3 ለ 2 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። ኔራዙሪዎቹ በፍጻሜው ባየር ሙኒክን በማሸነፍ ዋንጫውን ማንሳታቸው አይዘነጋም። በአጠቃላይ ሁለቱ ክለቦች በሻምፒዮንስ ሊጉ 12 ጊዜ ተገናኝተው ባርሴሎና 6 ጊዜ ሲያሸንፍ ኢንተር ሚላን ያሸነፈው 2 ጊዜ ብቻ ነው። 4 ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። ባርሴሎና ሻምፒዮንስ ሊጉን 5 ጊዜ፣ ኢንተር ሚላን ደግሞ 3 ጊዜ ማንሳት ችለዋል። በውድድሩ ለረጅም ጊዜ የካበተ ልምድ ያላቸው ሁለቱ ክለቦች የሚያደርጉት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ42 ዓመቱ ፈረንሳዊ ክሌመንት ቱርፓን ጨዋታውን በመሐል ዳኝነት ይመሩታል። ትናንት በሻምፒዮንስ ሊጉ በተደረገ የመጀመሪያ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ፒኤስጂ ከሜዳው ውጪ አርሰናልን 1 ለ 0 አሸንፏል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል
Apr 30, 2025 55
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 22/2017(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ። ስሑል ሽሬ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 9 ሰዓት፣ አዳማ ከተማ ከወልዋሎ አዲግራት ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። መርሃ ግብሩ ነገም ቀጥሎ ሲውል ኢትዮጵያ ቡና ከድሬዳዋ ከተማ፣ ፋሲል ከነማ ከሀድያ ሆሳዕና እና መቀሌ 70 እንደርታ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የ27ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ሚያዚያ 25 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚቆይ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል። ኢትዮጵያ መድን ሊጉን በ51 ነጥብ እየመራ ሲሆን ባህር ዳር ከተማ በ40 ነጥብ ይከተላል። ኢትዮጵያ ቡና በ39 እና መቻል በ38 ነጥብ ሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። ሃዋሳ ከተማ፣ አዳማ ከተማ፣ ስሑል ሽሬ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከ15ኛ እስከ 18ኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ ወራጅ ቀጠና ላይ ይገኛሉ። የሃዋሳ ከተማው ዓሊ ሱሌይማን በ12 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። የኢትዮጵያ መድኑ መሐመድ አበራ፣ የመቻል ሽመልስ በቀለ እና የአርባምንጭ ከተማው አህመድ ሁሴን በተመሳሳይ 10 ጎሎችን በማስቆጠር ይከተላሉ።
በተጠባቂው ጨዋታ ፒኤስጂ አርሰናልን አሸነፈ
Apr 29, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 21/2017 (ኢዜአ)፦በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ፒኤስጂ አርሰናልን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኡስማን ዴምቤሌ በአራተኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ግቧን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ተቀይረው የገቡት ብራድሊ ባርኮላ እና ጎንካሎ ራሞስ በጨዋታው ማገባደጃ ላይ ያመከኗቸው ግልጽ የግብ እድሎች የፒኤስጂን የአሸናፊነት ውጤት ይበልጥ ሊያሰፉ ይችሉ ነበር። ማይክል ሜሪኖ ከእረፍት መልስ ያስቆጠረው ጎል በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት(ቫር) ታይቶ ከጨዋታ ውጪ በመሆኑ ተሽሯል። ፒኤስጂ ከሜዳው ውጪ ወሳኝ ድል አግኝቷል። የመልስ ጨዋታው በቀጣዩ ሳምንት ረቡዕ ይደረጋል። ሁለተኛው የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ነገ በባርሴሎና እና ኢንተር ሚላን መካከል ይደረጋል።
የዓለም የእግር ኳስ አፍቃሪያን ዓይኖች ሁሉ ወደ ኤምሬትስ ያማትራሉ
Apr 29, 2025 101
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 21/2017 (ኢዜአ)፡- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር አርሰናል እና ፒኤስጂ ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ የተመልካቾችን ቀልብ አርፎበታል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 4 ሰዓት ላይ በኤምሬትስ ይካሄዳል። በሩብ ፍጻሜው አርሰናል የ15 ጊዜ የውድድሩን አሸናፊ ሪያል ማድሪድን በድንቅ ብቃት በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ተጋጣሚው ፒኤስጂ በበኩሉ በአስቶንቪላ ቢፈተንም የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብቷል። ሁለቱ ቡድኖች በመስከረም ወር 2017 ዓ.ም በሻምፒዮንስ ሊጉ ተገናኝተው አርሰናል በቡካዮ ሳካ እና ካይ ሃቫርትዝ ግቦች 2 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ቡድኖቹ እ.አ.አ 2016/17 በምድብ ደረጃ ተገናኝተው ሁለት ጊዜ ሳይሸናነፉ አቻ ተለያይተዋል። የለንደን እና የፓሪስ ከተማ ክለቦቹ በዛሬው ጨዋታ ተመጣጣኝ እና ለተመልካች አዝናኝ ፉክክር ያሳያሉ ተብሎ ይጠበቃል። የ45 ዓመቱ ስሎቬኒያዊ ስላቫኮ ቪንቺች ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ባርሴሎና ከኢንተር ሚላን ነገ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ናፖሊ የሊጉን መሪነት ከኢንተር ሚላን ተረከበ
Apr 27, 2025 107
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017 (ኢዜአ)፦ በጣልያን ሴሪአ የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ሰባት ጨዋታዎች ተደርገዋል። የዋንጫ ተፎካካሪዎቹ ኢንተር ሚላን እና ናፓሊ ጨዋታቸውን አካሂደዋል። በሳንሲሮ ስታዲየም ኢንተር ሚላን ሮማን አስተናግዶ 1 ለ 0 ተሸንፏል። አርጀንቲናዊው ማቲያስ ሱሌ የማሸነፊያ ግቧን አስቆጥሯል። በዲያጎ አርማንዶ ማራዶና ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ናፖሊ ቶሪኖን 2 ለ 0 አሸንፏል። ስኮት ማክቶሚናይ ሁለቱንም ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቶቹን ተከትሎ ናፖሊ በ74 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከኢንተር ሚላን ተረክቧል። ኢንተር ሚላን በ71 ነጥብ ወደ ሁለተኛ ደረጃ ዝቅ ብሏል። የአራት ሳምንት መርሃ ግብር የቀረው የጣልያን ሴሪአ ዋንጫውን ማን ያነሳል? የሚለው ጉዳይ ይበልጥ አጓጊ ሆኗል። በሌሎች ጨዋታዎች ጁቬንቱስ ሞንዛን፣ ኤሲ ሚላን ቬኔዚያን በተመሳሳይ 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ፊዮረንቲና ኢምፖሊን 2 ለ 1 እንዲሁም ኮሞ ጄኖዋን 1 ለ 0 ሲያሸንፉ አትላንታ ከሊቼ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
ሊቨርፑል የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ለ20ኛ ጊዜ ማንሳቱን አረጋገጠ
Apr 27, 2025 116
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሊቨርፑል ቶተንሃም ሆትስፐርስን 5 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሉዊስ ዲያዝ፣ መሐመድ ሳላህ፣ ኮዲ ጋፕኮ፣ አሌክሲስ ማካሊስተር እና የቶተንሃሙ ዴስትኒ ኡዶጊ በራሱ ግብ ላይ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ዶምኒክ ሶላንኪ ለስፐርስ ብቸኛዋን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ሊቨርፑል በ82 ነጥብ አራት ጨዋታ እየቀረ የሊጉን ዋንጫ ለ20ኛ ጊዜ ማንሳቱን አረጋግጧል። ይህም ሊቨርፑልን የሊጉን ዋንጫ በርካታ ጊዜ የማንሳት ክብረ ወሰንን ከታሪካዊ ባላንጣው ማንችስተር ዩናይትድ ጋር እንዲጋራ አድርጎታል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ37 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ቦርንማውዝ እና ማንችስተር ዩናይትድ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
ማንችስተር ሲቲ ለኤፍኤ ካፕ ፍጻሜ አለፈ
Apr 27, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ ሁለተኛ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ኖቲንግሃም ፎረስትን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በዌምብሌይ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሪኮ ሉዊስ እና ጆሽኮ ግቫርዲዮል ለሰማያዊዎቹ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ ለፍጻሜው አልፏል። በፍጻሜው ከክሪስታል ፓላስ ይገናኛል። ክሪስታል ፓላስ ትናንት አስቶንቪላን 3 ለ 0 ማሸነፉ ይታወቃል። ሁለቱ ክለቦች የፍጻሜ ጨዋታቸውን ግንቦት 9 2017 ዓ.ም በዌምብሌይ ስታዲየም ያደርጋሉ።
የህብረቱ አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር የሀገራቱን ሁለንተናዊ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ ነው - ኮሚሽነር ጀኔራል ደመላሽ ገብረሚካዔል
Apr 27, 2025 119
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር ከውድድርነት ባለፈ የሀገራቱን ሰላምና ሁለንተናዊ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ መሆኑን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀኔራል ደመላሽ ገብረሚካዔል ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ የተመሰረተበትን 116ኛ ዓመት በማስመልከት አምስተኛው የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር የመክፈቻ መርሃ ግብር በሻምበል አበበ ቢቂላ ስታዲየም ተካሂዷል። የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀኔራል ደመላሽ ገብረሚካዔል በዚሁ ወቅት፤ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ባለፉት የለውጥ አመታት በርካታ የሪፎርም ስራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል ብለዋል፡፡ ሪፎርሙን ተከትሎ በሰው ሐብት ልማት፣ በቴክኖሎጂ፣ በሎጀስቲክስ፣ በምርመራ፣ በወንጀል መከላከልና በግንኙነት ዘርፎች አመርቂ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚህም የሀገራችን አስተማማኝ ሰላምና ደህንነት ማረጋገጥ መቻሉን ነው የገለጹት፡፡ ኮሚሽነር ጀኔራል ደመላሽ ገብረሚካዔል በውድድሩ ኢትዮጵያን ጨምሮ ኬንያ፣ ሩንዳ፣ ዩጋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ ደቡብ ሱዳንና ጅቡቲ ተሳታፊ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የውድድሩ ዋና አላማ የሀገራቱን ግንኙነት ይበልጥ በማጠናከር የምስራቅ አፍሪካን ሰላምና ደህንነት በትብብርና በቅንጅት ለማስከበር መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ወንድማማችነትን የማጠናከር፣ የእርስ በእርስ ልምድ ለመለዋወጥና ተተኪ ስፖርተኞችን የማፍራት አላማ እንዳለውም ተናግረዋል፡፡ የ116ኛውን ብሔራዊ የፖሊስ በዓል አሁን ላይ በደረስንበትን ስኬት ሳንዘናጋ ለቀጣይ ተልዕኮ የምንዘጋጅበት ነው ብለዋል፡፡ በኬንያ ናይሮቢ የኢንተርፖል ቀጣናዊ ቢሮ ተወካይ ቦስኮ ጋሂጂ፥ በበኩላቸው፤ ዛሬ የተጀመረው ስፖርታዊ ውድድር ከስፖርት ጨዋታነት ባለፈ ቀጣናዊ ትስስርን በማጎልበት የተደራጁ ወንጀለኞችንና ሽብርተኝነትን ለመከላከል ጉልህ ድርሻ ያለው ነው ብለዋል፡፡ በመሆኑም በቀጣይ የቀጣናውን ሀገራት ሁለንተናዊ ትስስር በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ላይ በጋራና በትብብር መስራት እንደሚገባ ነው የተናገሩት፡፡ 5ኛው የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት ስፖርታዊ ውድድር እስከ ሚያዚያ 25 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ይካሄዳል።
ኢትዮጵያ በሴቶች 1ሺህ 500 ሜትር የሩጫ ውድድር ሁሉንም ሜዳሊያዎች አሸነፈች
Apr 27, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ በ5ኛው የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅት ስፖርታዊ ውድድር ኢትዮጵያ በሴቶች 1ሺህ 500 ሜትር የሩጫ ውድድር ሁሉንም ሜዳሊያዎች አሸነፈች። የኢትዮጵያ ፖሊስ የተመሰረተበትን 116ኛ ዓመት በዓል በማስመልከት 5ኛው የምስራቅ አፍሪካ የፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር የመክፈቻ መርሃ ግብር ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተከናውኗል። በመክፈቻ መርሃ ግብሩ የሴቶች 1ሺህ 500 ሜትር እና የወንዶች የ400 ሜትር የዱላ ቅብብል የሩጫ ውድድር ተካሂዷል። በሴቶች 1ሺህ 500 ሜትር የሩጫ ውድድር ኢትዮጵያውያኑ ወርቅነሽ መሰለ፣ የኔነሽ ሺመክት እና ማተቤ ፍቃዱ በቅደም ተከተል ከ1ኛ እስከ 3ኛ በመውጣት ሁሉንም ሜዳሊያዎች ወስደዋል። በወንዶች የ400 ሜትር የዱላ ቅብብል ውድድር ደግሞ ኬንያ አንደኛ ኢትዮጵያ ሁለተኛ እንዲሁም ታንዛኒያ ሶስትኛ በመውጣት ውድድሩን አሸንፈዋል። አሸናፊዎቹ አትሌቶች የሜዳሊያ ሽልማታቸውን ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ እጅ ተቀብለዋል። ኢትዮጵያን ጨምሮ ሰባት ሀገራት የሚሳተፉበት 5ኛው የምስራቅ አፍሪካ የፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር እስከ ሚያዚያ 25/2017 ዓ.ም ድረስ ይቀጥላል።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ሲዳማ ቡና ለፍፃሜ ደረሰ
Apr 27, 2025 55
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ ግማሽ ፍፃሜ ውድድር ሲዳማ ቡና መቻልን በመለያ ምት 7ለ6 በማሸነፍ ለፍፃሜ አልፏል። ሁለቱ ክለቦች መደበኛውን የጨዋታ ክፍለ ጊዜ 0ለ0 በማጠናቀቃቸው ነው ወደ መለያ ምት ያመሩት። በፍፃሜው ሲዳማ ቡና ከወላይታ ድቻ ጋር የሚገናኙ ሲሆን የፍፃሜ ጨዋታው ግንቦት 30/2017 ዓ.ም እንደሚካሄድ ተገልጿል። የውድድሩ አሸናፊ ኢትዮጵያን ወክሎ በአፍሪካ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ተሳታፊ እንደሚሆንም ይታወቃል።
በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ማንችስተር ዩናይትድ እና በርማውዝ አቻ ተለያዩ
Apr 27, 2025 45
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ በ34ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ ከሜዳው ውጪ ተጉዞ ከበርንማውዝ ጋር ያደረገውን ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት አጠናቋል፡፡ የበርንማውዝን ግብ ሴሜኒዮ በመጀመሪያው አጋማሽ ሲያስቆጥር፤ ሆይሉንድ ማንቼስተር ዩናይትድን አቻ ያደረገች ግብ በጨዋታው መጠናቀቂያ አስቆጥሯል፡፡ ውጤቱን ተከትሎ በርንማውዝ በ50 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ፤ ማንችስተር ዩናይትድ በ39 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡ የሊጉ ጨዋታ ሲቀጥል ተጠባቂው የሊቨርፑል እና ቶተንሀም ሆትስፐር ጨዋታ በአንፊልድ ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ይደረጋል፡፡ ከጨዋታው አስቀድሞ የሊቨርፑል ደጋፊዎች በአንፊልድ አካባቢ ደማቅ የድጋፍ እንቅስቃሴ እያሳዩ ይገኛሉ፡፡
በሴቶች የለንደን ማራቶን ውድድር አትሌት ትዕግስት አሰፋ አሸነፈች
Apr 27, 2025 64
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ በተጠባቂው የሴቶች ለንደን ማራቶን ውድድር አትሌት ትዕግስት አሰፋ አሸንፋለች። በ45ኛውን የለንደን ማራቶን የሴቶች ምድብ ውድድር የፓሪስ ኦሎምፒክ የብር ሜዳልያ ባለቤቷ አትሌት ትዕግስት አሰፋ በበላይነት ማሸነፏን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ አመላክቷል። አትሌት ትዕግስት አሰፋ ውድድሩን 2:15.50 በመግባት በአንደኝነት ስታሸንፍ ኬንያዊቷ አትሌት ጆይስሊን ጄፕኮስጊ ሁለተኛ እንዲሁም ኔዘርላንዳዊቷ አትሌት ሲፈን ሀሰን ሶስተኛ ደረጃ በመያዝ አጠናቀዋል።
ሞገስ ጥዑማይ እና ገመኔ ማሚቴ የኢትዮጵያ ታምርት የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር አሸናፊ ሆኑ
Apr 27, 2025 58
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድርን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ክለብ ሞገስ ጥዑማይ በወንዶች እንዲሁም የኮዬ ፈጬ ክፍለ ከተማዋ ገመኔ ማሚቴ በሴቶች አሸናፊ ሆነዋል። መነሻና መድረሻውን በመስቀል አደባባይ ያደረገው 4ኛ ዓመት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የ2017 ኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ የ10 ኪ.ሜ የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር ተካሂዷል። በዝግጅቱ ላይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን(ዶ/ር)፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ጃንጥራር ዓባይን ጨምሮ የፌዴራልና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በውድድሩም የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ክለብ ሞገስ ጥዑማይ በወንዶች እንዲሁም የኮዬ ፈጬ ክፍለ ከተማዋ ገመኔ ማሚቴ በሴቶች የኢትዮጵያ ታምርት የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር አሸነፊ ሆነዋል። በዚህም በ10 ኪሎ ሜትር የኢትዮጵያ ታምርት የወንዶች የሩጫ ውድድር፦ 1ኛ. ሞገስ ጥዑማይ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ የወርቅ ሜዳሊያ እና የ300 ሺህ ብር፣ 2ኛ.ጅራታ ሌሊሳ በግል የብር ሜዳሊያና የ200 ሺህ ብር እንዲሁም 3ኛ. ሲዳ አማና ከሸገር ከተማ የነሀስ ሜዳሊያ እና የ100 ሺህ ብር ሽልማት አሸናፊ በመሆን ከኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል እና ከኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡሉልታ እጅ የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ተረክበዋል። በተመሳሳይ በ10 ኪሎ ሜትር የኢትዮጵያ ታምርት የሴቶች የሩጫ ውድድር፦ 1ኛ. ገመኔ ማሚቴ ከኮዬ ፈጬ ክፍለ ከተማ የወርቅ ሜዳሊያ እና የ300 ሺህ ብር፤ 2ኛ.አበዙ ከበደ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የብር ሜዳሊያና የ200 ሺህ ብር እንዲሁም፤ 3ኛ. ማርታ አለማየሁ በግል የነሀስ ሜዳሊያ እና የ100 ሺህ ብር አሸናፊ በመሆን ከባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ እና ከአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ጃንጥራር ዓባይ ዕጅ የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ተረክበዋል። የሩጫ ውድድሩን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ሲሆን ውድድሩም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 4ኛ ዓመት ዝግጅትን አስመልክቶ የተሰናዳ መሆኑ ተገልጿል።
የሊጉ መሪ ሊቨርፑል የዋንጫ ባለቤትነቱን ያረጋግጥ ይሆን?
Apr 27, 2025 60
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሊቨርፑል ከቶተንሃም ሆትስፐርስ ጋር ይጫወታል። ጨዋታው ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ላይ በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ይደረጋል። ሊቨርፑል በ79 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ37 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ቀያዮቹ በጨዋታው ካሸነፉ ወይም አቻ ከወጡ የሊጉን ዋንጫ ለ20ኛ ጊዜ ማንሳታቸውን ያረጋግጣሉ። ይህም ሊቨርፑልን የሊጉን ዋንጫ በርካታ ጊዜ የማንሳት ክብረ ወሰንን ከታሪካዊ ባላንጣው ማንችስተር ዩናይትድ ጋር እንዲጋራ ያደርገዋል። በሌላኛው የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ቦርንማውዝ ከማንችስተር ዩናይትድ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ ሲዳማ ቡና ከመቻል ይጫወታሉ
Apr 27, 2025 52
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና ከመቻል ዛሬ ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ በሃዋሳ ከተማ ይደረጋል። በሩብ ፍጻሜው ሲዳማ ቡና ሀድያ ሆሳዕናን፣ መቻል ኢትዮጵያ መድንን በመርታት ለዛሬው ጨዋታ ደርሰዋል። የሁለቱ ቡድኖች አሸናፊ ከወላይታ ድቻ ጋር ለፍጻሜው ይገናኛል። ወላይታ ድቻ ትናንት ሸገር ከተማን 2 ለ 0 በማሸነፍ ለፍጻሜ ማለፉ ይታወቃል። የኢትዮጵያ ዋንጫ አሸናፊ ክለብ ኢትዮጵያን ወክሎ በቀጣዩ ዓመት በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል።
ኖቲንግሃም ፎረስት እና ማንችስተር ሲቲ በኤፍኤ ካፕ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል
Apr 27, 2025 48
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017(ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ ሁለተኛ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ኖቲንግሃም ፎረስት ከማንችስተር ሲቲ ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 12 ሰዓት ከ30 ላይ በዌምብሌይ ስታዲየም ይካሄዳል። ኖቲንግሃም ፎረስት በሩብ ፍጻሜው ብራይተንን እንዲሁም ማንችስተር ሲቲ ቦርንማውዝን አሸንፈዋል። በኤፍኤ ካፕ ተሳትፏቸው ታሪክ ኖቲንግሃም ፎረስት ሁለት ጊዜ ዋንጫውን ሲያነሳ ማንችስተር ሲቲ ሰባት ጊዜ በማንሳት ብልጫውን ይወስዳል። በተጨማሪም ማንችስተር ሲቲ በውድድሩ 6 ጊዜ እና ኖቲንግሃም ፎረስት 1 ጊዜ ለፍጻሜ ደርሰው ሽንፈት አስተናግደዋል። የሁለቱ ክለቦች አሸናፊ ከክሪስታል ፓላስ ጋር በፍጻሜው ይጫወታል። ክሪስታል ፓላስ አስቶንቪላን ትናንት 3 ለ 0 በማሸነፍ ለፍጻሜው አልፏል። የ40 ዓመቱ ማይክል ኦሊቨር የሁለቱን ክለቦች ተጠባቂ ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
ተጠባቂው የለንደን ማራቶን
Apr 27, 2025 53
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017 (ኢዜአ)፡- 45ኛው የለንደን ማራቶን ዛሬ ረፋድ ላይ ይካሄዳል። በሁለቱም ጾታዎች የሚደረጉ የዓለም የአትሌቲክስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። በሴቶች አትሌት ትዕግስት አሰፋ እና አትሌት ሲፋን ሀሰን የሚያደርጉት ፉክክር በጉጉት እንደሚጠበቅ የዓለም አትሌቲክስ መረጃ ያመለክታል። ሁለቱ አትሌቶች በፓሪስ በተካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በማራቶን ውድድር እስከ መጨረሻው እልህ አስጨራስ ፉክክር አድርገው ሲፋን አንደኛ፣ ትዕግስት ሁለተኛ ደረጃን ይዘው ማጠናቀቃቸው የሚታወስ ነው። አትሌቶቹ ከኦሊምፒኩ መልስ ዳግም በወሳኝ የአትሌቲክስ መድረግ ላይ ተገናኝተዋል። አትሌት ትዕግስት 2 ሰዓት ከ11 ደቂቃ ከ53 ሴኮንድ በርቀቱ የዓለም ሁለተኛ ፈጣን ሰዓት ባለቤት ናት። ሲፋን 2 ሰዓት ከ13 ደቂቃ ከ44 ሴኮንድ የዓለም ሶስተኛ ፈጣን ሰዓትን አስመዝግባለች። ኬንያዊቷ የማራቶን የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት ሩት ቼፕጌቲች እና የባለፈው ዓመት የውድድሩ አሸናፊ የሆነችው ሌላኛዋ ኬንያዊ አትሌት ፔሬዝ ቼፕቺርቺር በውድድሩ ላይ አይሳተፉም። ሌላኛዋ ኬንያዊ ጆይስሊን ጄፕኮስጌ የሀገሬው ሰዎች ተስፋ የጣሉበት አትሌት ናት። በወንዶች በፓሪስ የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በማራቶን የወርቅ ሜዳሊያ ያገኘው አትሌት ታምራት ቶላ እንዲሁም ኬንያዊው ኢሊውድ ኪፕቾጌ እና ሌላኛው የሀገሩ ልጅ አሌክሳንዳር ሙቲሶ ሙናዮ የማሸነፉን የቅድሚያ ግምት አግኝተዋል። ሙናዮ የባለፈው ዓመት የውድድሩ አሸናፊ ነው። ዩጋንዳዊው ጃኮብ ኪፕሊሞ ሌላኛው ተጠባቂ አትሌት ነው። አንጋፋው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በጉዳት ምክንያት ከውድድሩ ውጪ መሆኑ የሚታወስ ነው። በሁለቱም ጾታዎች የሚያሸንፉ አትሌቶች በተመሳሳይ የ55 ሺህ የአሜሪካን ዶላር ሽልማት ያገኛሉ። እ.አ.አ በ1981 የተጀመረው የለንደን ማራቶን በዓለም አትሌቲክስ የወርቅ ደረጃ የተሰጠው የጎዳና ላይ ውድድር ሲሆን በዓለም ላይ ተጠባቂ ከሆኑ ውድድሮች መካከል በዋናነት የሚጠቀስ ነው።
ባርሴሎና የኮፓ ዴል ሬይ ዋንጫን ለ32ኛ ጊዜ አነሳ
Apr 26, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2017(ኢዜአ)፦ በስፔን የኮፓ ዴል ሬይ የፍጻሜ ጨዋታ ባርሴሎና ሪያል ማድሪድን 3 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በዴላ ካርቱጃ ስታዲየም በተካሄደው የፍጻሜ ጨዋታ ፔድሪ፣ ፌራን እና ኩንዴ ለባርሴሎና ግቦቹን ሲስቆጥሩ ለማድሪድ ደግሞ ኪሊያን ምባፔ እና ኦሪየል ችዌሜኒ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጨዋታው በመደበኛው 90 ደቂቃ ሁለት አቻ በመጠናቀቁ ቡድኖቹ ወደ ጭማሪ ሰዓት አምርተዋል። ጁለስ ኩንዴ በ116ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ባርሴሎናን አሸናፊ አድርጓል። አንቶኒ ሩዲገር በ123ኛው ደቂቃ ቀይ ካርድ ተመልክቷል። ውጤቱን ተከትሎ ባርሴሎና የስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ ባለቤት ሆኗል። የውድድሩ የበርካታ ጊዜ ባለክብር ዋንጫውን ለ32ኛ ጊዜ ከፍ አድርጓል።