ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሃዋሳ ከተማ ድሬዳዋ ከተማን አሸነፈ
Nov 7, 2025 35
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ በቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ስራ ይርደው እና ፀሐይነሽ ጁላ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሃዋሳ ከተማ በውድድር ዓመቱ አራተኛ ድሉን በማስመዝገብ በ12 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በአንጻሩ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በሶስት ነጥብ ከ10ኛ ደረጃ ወደ 11ኛ ዝቅ ብሏል። የአምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ቀጥሎ ሲውል አዲስ አበባ ከተማ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት፣ ልደታ ክፍለ ከተማ ከሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከቀኑ 9 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል
Nov 7, 2025 57
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከነገሌ አርሲ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችንም ሲያስቆጥር አንድ ጎል አስተናግዷል። ቡድኑ በ10 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። አዲስ አዳጊው አርሲ ነጌሌ በውድድር ዓመቱ ባከናወናቸው አራት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ አራት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በሁለት ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ጨዋታው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በድል ጉዞው ለመቀጠል ነጌሌ አርሲ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ የሚያደርጉት ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር ወላይታ ድቻ ከመቀሌ 70 እንደርታ ከቀኑ 10 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወላይታ ድቻ በሊጉ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። በጨዋታዎቹ አንድ ግብ ብቻ ሲያስቆጥር ስድስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ በሊጉ እስከ አሁን ባካሄዳቸው አራት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ሶስት ጊዜ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። አራት ግቦችን ሲያስቆጥር ስምንት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በአንድ ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ቡድኖቹ የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ የሚያደርጉት ፍልሚያ ነው። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። መቻል ሊጉን በ10 ነጥብ እየመራ ይገኛል። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የሃዋሳ ከተማ ተጫዋቾቹ ጌታነህ ከበደ እና ያሬድ ብሩክ፣ የፋሲል ከነማው በረከት ግዛው እና የመቻሉ መሐመድ አበራ በተመሳሳይ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር በጋራ ይመራሉ።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል
Nov 7, 2025 57
አዲስ አበባ ፤ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የአምስተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይደረጋሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ድሬዳዋ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ ይጫወታሉ። ድሬዳዋ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። ቡድኑ በሶስት ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሃዋሳ ከተማ ከአራት ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈትን አስተናግዷል። ሃዋሳ ከተማ በዘጠኝ ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አዲስ አበባ ከተማ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። አዲስ አበባ ከተማ በሶስት ነጥብ 12ኛ፣ ሸገር ከተማ በስድስት ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዘዋል። የዕለቱ የመጨረሻ መርሃ ግብር ልደታ ክፍለ ከተማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክን ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ያገናኛል። ልደታ ክፍለ ከተማ በአምስት ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን የያዘ ሲሆን ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ12 ነጥብ ሊጉን ይመራል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ አምስተኛ ሳምንት እስከ ጥቅምት 30 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን በስምንት ግቦች ትመራለች። የልደታ ክፍለ ከተማዎቹ ቃልኪዳን ጥላሁንና ረድኤት ዳንኤል፣ ቱሪስት ለማ፣ ቤተልሄም መንተሎ እና ትዕግስት ወርቁ ከመቻል፣ ምትኬ ብርሃኑ ከሲዳማ ቡና፣ ፊርማዬ ከበደ ከድሬዳዋ ከተማ እና የሸገር ከተማዋ ሰናይት ኡራጎ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን በማስቆጠር ይከተላሉ።
ኢትዮጵያ በዓለም የጠረጴዛ ቴኒስ ሻምፒዮና ትሳተፋለች
Nov 6, 2025 108
አዲስ አበባ ፤ጥቅምት 27/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ በለንደን በሚካሄደው የዓለም የቡድን የጠረጴዛ ቴኒስ ሻምፒዮና በሴቶች ተሳትፎ እንደምታደርግ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ። ሻምፒዮናው የዓለም አቀፍ የጠረጴዛ ቴኒስ ፌዴሬሽን የተመሰረተበትን 100ኛ ዓመት በማስመልከት ከሚያዚያ 20 እስከ ግንቦት 2 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ በሁለቱም ጾታዎች በአጠቃላይ 64 ቡድኖች ይሳተፋሉ። የኢትዮጵያ ጠረጴዛ ቴኒስ የሴቶች ብሄራዊ ቡድን በዓለም የቡድን የጠረጴዛ ቴኒስ ሻምፒዮና እንደሚሳተፍ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር ገልጿል። ብሄራዊ ቡድኑ የሚሳተፈው እ.አ.አ በ2025 በነበረው ዓለም አቀፍ የጠረጴዛ ቴኒስ ደረጃ አማካኝነት መሆኑ ተመላክቷል። ቡድኑ እ.አ.አ በ2024 በተካሄደው ሻምፒዮና ላይ ተሳትፎ አድርጎ ነበር። የኢትዮጵያ ተሳትፎ ለጠረጴዛ ቴኒስ ስፖርት እድገት የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ሚኒስቴሩ ገልጿል።
የሀላባ ኢንተርናሽናል ስታዲየም የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ እየተጠናቀቀ ነው
Nov 6, 2025 126
ቁሊቶ፤ጥቅምት 27/2018 (ኢዜአ)፡- የሀላባ ኢንተርናሽናል ስታዲየም የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ የዞኑ አስተዳደር ገለፀ፡፡ የስታዲየሙን የግንባታ ሂደት በተመለከተ ለኢዜአ ማብራሪያ የሰጡት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ልዩ አማካሪ አቶ ከድር ቆሮቾ እንደገለፁት፤ በማህበረሰብ ተሳትፎ እየተገነባ ያለው የቁሊቶ ኢንተርናሽናል ስታዲየም ግንባታ እየተፋጠነ ነው፡፡ ግንባታውን በሶስት ምዕራፎች ለማጠናቀቅ ታስቦ ወደ ተግባር የተገባ መሆኑን ጠቁመው የመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ እየተጠናቀቀ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የእግር ኳስ ሜዳውን ሰው ሰራሽ ሳር የማልበስ፤ ደረጃውን የጠበቀ የመሮጫ መምና የተመልካች መቀመጫ የመግጠም ስራዎች በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡ በዓለም አቀፍ ስታንዳርድ ግንባታው እየተከናወነ ያለው የቁሊቶ ኢንተርናሽናል ስታዲየም ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት እንደተመደበለትም አስረድተዋል፡፡ የስታዲየሙ ግንባታ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ነው ያስረዱት፡፡ የስታዲየሙ የእግር ኳስ ሜዳውና የመሮጫ ትራኩ ግንባታ በፊፋ እና በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አማካኝነት በተደረገ ምዘና በጥሩ ሂደት ላይ እየተከናወነ እንደሆነ ግብረ መልስ እንደተሰጠም ገልጸዋል፡፡ ከስታዲየሙ ግንባታ ጎን ለጎንም እንግዶችን ለመቀበል የሚያስችሉ የሆቴሎች ግንባታ ለማከናወን ከባለሀብቶች ጋር መግባባት ላይ መደረሱንም ገልፀዋል፡፡ በሶስት ምዕራፎች ተከፍሎ ግንባታው እየተፋጠነ የሚገኘው የሀላባ ኢንተርናሽናል ስታዲየም የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)ን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ሐምሌ 10/2016 ዓ.ም ስራው በይፋ መጀመሩ ይታወሳል።
ማንችስተር ሲቲ ቦሩሲያ ዶርትሙንድን አሸነፈ
Nov 6, 2025 115
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 27/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጠባቂ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ቦሩሲያ ዶርትሙንድን 4 ለ 1 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ፊል ፎደን ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አርሊንግ ሃላንድ እና ራያን ቼርኪ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ዋልዴማር አንቶን ለዶርትሙንድ ግቧን አስቆጥሯል። ፎደን በጨዋታው ላይ ድንቅ ብቃቱን ያሳየ ሲሆን የጨዋታው ኮከብ ተብሎ ተመርጧል። ሃላንድ ዘንድሮ በሁሉም ውድድሮች ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ 18 ከፍ አድርጓል። ድሉን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ በ10 ነጥብ ደረጃውን ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። ቦሩሲያ ዶርትሙንድ በሰባት ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። በሌሎች ጨዋታዎች ባርሴሎና ከክለብ ብሩዥ ጋር ሶስት አቻ ተለያይቷል። ጃኮብ ፎርብስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኒኮሎ ትሬሶልዲ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ፌራን ቶሬስ፣ ላሚን ያማል እና የክለብ ብሩዡ ክሪስቶስ ዞሊስ በራሱ ላይ ግቦቹን ለባርሴሎና ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኒውካስትል ዩናይትድ በዳን በርን እና ጆኢሊንተን ግቦች አትሌቲኮ ቢልባኦን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሳንሲሮ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኢንተር ሚላን ካይራት አልማቲን 2 ለ 1 አሸንፏል። ላውታሮ ማርቲኔዝ እና ካርሎስ አጉስቶ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኦፍሪ አራድ ለካይራት ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጋላታሳራይ አያክስን 3 ለ 0፣ ባየር ሌቨርኩሰን ቤኔፊካን እና አትላንታ ማርሴይን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
በሻምፒዮንስ ሊጉ ካራባግ እና ቼልሲ አቻ ተለያዩ
Nov 5, 2025 144
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መርሃ ግብር ካራባግ እና ቼልሲ ያደረጉት ጨዋታ ሁለት በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ማምሻውን በቶፊክ ባህራሞቭ አዲና ሬስሪፐብሊክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሊያንድሮ አንድራዴ በጨዋታ እና ማርኮ ያንኮቪች በፍጹም ቅጣት ምት ለካራባግ ግቦቹን አስቆጥረዋል። እስቴቫኦ እና አሌሃንድሮ ጋርናቾ ለቼልሲ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ቼልሲ እና ካራባግ በተመሳሳይ ሰባት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው 10ኛ እና 12ኛ ደረጃን ይዘዋል። በሌላኛው ጨዋታ ፓፎስ ቪያሪያልን 1 ለ 0 አሸንፏል። ዴሪክ ላካሰን የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች በህዳር ወር መጀመሪያ ይካሄዳሉ
Nov 5, 2025 121
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 26/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ደልድል ዛሬ ይፋ አድርጓል። በዚሁ መሰረት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሲዳማ ቡና፣ ድሬዳዋ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ፣ መቀሌ 70 እንደርታ ከፋሲል ከነማ፣ ምድረገነት ሽሬ ከመቻል፣ ወላይታ ድቻ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ፣ አርባምንጭ ከተማ ከቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከኢትዮጵያ መድን፣ ሀዲያ ሆሳዕና ከነጌሌ አርሲ፣ ባህር ዳር ከተማ ከሸገር ከተማ እና አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና ይጫወታሉ። ሀላባ ከተማ ከቦዲቲ ከተማ፣ ደብረብርሃን ከተማ ከአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ፣ ቢሾፍቱ ከተማ ከደሴ ከተማ፣ ሐረር ከተማ ከአቃቂ ክፍለ ከተማ፣ ንብ ከየካ ክፍለ ከተማ እና ቤንችማጂ ቡና ከጋሞ ጨንቻ ሌሎች የሚደረጉ ጨዋታዎች ናቸው። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ከህዳር 2 እስከ 4 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ጨዋታዎቹ አዲስ አበባ ስታዲየም፣ ሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም፣ ሃዋሳ አርቴፊሻል ሜዳ እና ጅማ ስታዲየም ይደረጋሉ። በመጀመሪያው ዙር ውድድር የከፍተኛ ሊግ ክለቦች ብቻ የተሳተፉ ሲሆን አሸናፊ ቡድኖች በሁለተኛው ዙር ከኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ቡድኖች ጋር በመቀላቀል ይጫወታሉ። ወላይታ ድቻ የወቅቱ የኢትዮጵያ ዋንጫ አሸናፊ ነው። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሚያሸንፍ ቡድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል።
በሻምፒዮንስ ሊጉ ማንችስተር ሲቲ ከቦሩሲያ ዶርትሙንድ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Nov 5, 2025 116
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 26/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዛሬ ዘጠኝ ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በኢትሃድ ስታዲየም ማንችስተር ሲቲ ከቦሩሲያ ዶርትሙንድ ምሽት 5 ሰዓት ላይ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠቃሽ ነው። ቦሩሲያ ዶርትሙንድ እና ማንችስተር ሲቲ በተመሳሳይ ሰባት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ስምንተኛ እና ዘጠነኛ ደረጃን ይዘዋል። ክለቦቹ በሻምፒዮንስ ሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለሰባተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ስድስት ጨዋታዎች ማንችስተር ሲቲ ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ዶርትሙንድ አንድ ጊዜ አሸንፏል። ሁለት ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በጨዋታዎቹ ማንችስተር ሲቲ ሰባት ግቦችን ሲያስቆጥር ዶርትሙንድ አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ዶርትሙንድ ሲቲን ያሸነፈው እ.አ.አ በ2012/13 የውድድር ዓመት ሲሆን በምድብ ተገናኝተው 1 ለ 0 ማሸነፍ ችሏል። ሁለቱ ክለቦች ለመጨረሻ ጊዜ በውድድሩ የተገናኙት እ.አ.አ በ2022/23 ነው። በወቅቱ ባደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ቡድኖቹ ባለፈው የውድድር ዓመት ከነበራቸው ደካማ ብቃት በማገገም ዘንድሮ ጥሩ እንቅስቃሴ እያደረጉ ይገኛል። በዛሬውም ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። የ44 ዓመቱ ፖላንዳዊ ሲሞን ማርሲኒያክ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ክለብ ብሩዥ ከባርሴሎና፣ ቤኔፊካ ከባየር ሌቨርኩሰን፣ ኢንተር ሚላን ከካይራት አልማቲ፣ ማርሴይ ከአትላንታ፣ ኒውካስትል ዩናይትድ ከአትሌቲኮ ቢልባኦ እና አያክስ ከጋላታሳራይ በተመሳሳይ ምሽት 5 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ላይ ካራባግ ከቼልሲ እና ፓፎስ ኤፍሲ ከቪያሪያል ይጫወታሉ።
በሻምፒዮንስ ሊጉ ተጠባቂ ጨዋታዎች ሊቨርፑል ሪያል ማድሪድን ባየር ሙኒክ ፒኤስጂን አሸንፈዋል
Nov 5, 2025 140
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 25/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ማምሻውን ሰባት ጨዋታዎች ተደርገዋል። በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አሌክሲስ ማካሊስተር በ61ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ሊቨርፑል በርካታ የግብ እድሎችን ቢፈጥርም በጨዋታው ድንቅ ብቃቱን ያሳየው የሪያል ማድሪድ ግብ ጠባቂ ቲቦ ኮርቶዋ አድኗቸዋል። የቀድሞው የሊቨርፑል ተጫዋች ትሬንት አሌክሳንደር አርኖልድ ተቀይሮ በመግባት ያደገበትን ክለብ ገጥሟል። ውጤቱን ተከትሎ ሊቨርፑል በውድድሩ ሶስተኛ ድሉን ሲያስመዘግብ ሪያል ማድሪድ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በፓርክ ደ ፕሪንስ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው ተጠባቂ ጨዋታ ባየር ሙኒክ የወቅቱን የውድድሩን አሸናፊ ፒኤስጂን 2 ለ 1 አሸንፏል። ሉዊስ ዲያዝ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። ዲያዝ በጨዋታው በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ጆአኦ ኔቬስ ለፒኤስጂ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የባሎን ዶር አሸናፊው ኡስማን ዴምቤሌ ባጋጠመው ጉዳት በ25ኛው ደቂቃ ላይ ተቀይሮ ለመውጣት ተገዷል። ባየር ሙኒክ ነጥቡን ወደ 12 ከፍ በማድረግ መሪነቱን ከአርሰናል ተረክቧል። ፒኤስጂ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በሌሎች ጨዋታዎች ቶተንሃም ሆትስፐርስ ኤፍሲ ኮፐንሃገንን 4 ለ 0 እና አትሌቲኮ ማድሪድ ዩኒየን ሴይንት ጊሎስን 3 ለ 1 አሸንፈዋል። ሞናኮ ቦዶ ግሊምትን በተመሳሳይ 1 ለ 0 ማሸነፍ ችሏል። ጁቬንቱስ ከስፖርቲንግ ሊዝበን፣ ኦሎምፒያኮስ ከፒኤስቪ አይንድሆቨን በተመሳሳይ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
አርሰናል ስላቪያ ፕራግን በማሸነፍ የሻምፒዮንስ ሊጉን የመሪነት ደረጃ ይዟል
Nov 4, 2025 124
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 25/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መርሃ ግብር አርሰናል ስላቪያ ፕራግን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በፎርቹና አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማይክል ሜሪኖ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ቡካዮ ሳካ ቀሪዋን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ አሳርፏል። አርሰናል በኳስ ቁጥጥር ብልጫ የወሰደ ሲሆን በርካታ የግብ እድሎችንም ፈጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ አርሰናል የሻምፒዮንስ ሊግ የሊግ ውድድር ፎርማት ደረጃን በ12 ነጥብ መምራት ጀምሯል። መድፈኞቹ ባለፉት ስምንት ጨዋታዎች ግብ አልተቆጠረባቸውም። ተቀይሮ የገባው የአርሰናሉ ማክስ ዳውማን በ15 ዓመት 308 ቀናት በመጫወት በሻምፒዮንስ ሊጉ ታሪክ የተሰለፈ በእድሜ ትንሹ ወጣት ተጫዋች ሆኗል። በውድድሩ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ስላቪያ ፕራግ በሁለት ነጥብ 30ኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሃ ግብር ናፖሊ እና ኢንትራክት ፍራንክፈርት ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል።
መቻል ዳግም የሊጉን መሪነት ተረከበ
Nov 4, 2025 109
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 25/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት መቻል ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ መሐመድ አበራ እና ብሩክ ማርቆስ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሊጉ ሶስተኛ ድሉን ያሳካው መቻል በ10 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ተረክቧል። በአንጻሩ በሊጉ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በአንድ ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቀን ላይ በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0፣ አዳማ ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የአራተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የአምስተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከጥቅምት 28 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እንደሚካሄዱ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድል ቀንቶታል
Nov 4, 2025 99
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 25/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ይርጋጨፌ ቡናን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ እፀገነት ግርማ፣ መሳይ ተመስገን፣ ታሪኳ ዴቢሶ እና ንግስት በቀለ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ጨዋታውን ያደረገው ንግድ ባንክ ድል ቀንቶታል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ተሳትፎ ምክንያት የመጀመሪያ ሶስት ሳምንታት ጨዋታዎቹን አላደረገም። ጨዋታዎቹ በተስተካካይ መርሃ ግብርነት ተይዘዋል። አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል። ቀን ላይ በተደረገ ጨዋታ መቻል እና ሲዳማ ቡና ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የአራተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል።
በፕሪሚየር ሊጉ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና አዳማ ከተማ ድል ቀንቷቸዋል
Nov 4, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 25/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ጨዋታዎች በመካሄድ ይገኛሉ። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ዩጋንዳዊው ሳይመን ፒተር እና የድሬዳዋ ከተማ ድልአዲስ ገብሬ በራሱ ግብ ላይ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ሲያስመዘግብ ድሬዳዋ ከተማ ሁለተኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው መርሃ ግብር አዳማ ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። ወጣቱ አጥቂ ቢኒያም አይተን በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ አሳርፏል። አዳማ ከተማ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ሲያገኝ አርባምንጭ ከተማ በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ሽንፈት አስተናግዷል። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ ማሸነፍ አልቻለም። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቻል ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ መቻል እና ሲዳማ ቡና አቻ ተለያዩ
Nov 4, 2025 93
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 25/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አራተኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቻል እና ሲዳማ ቡና ያደረጉት ጨዋታ ሁለት አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቱሪስት ለማ ሁለቱን ግቦች ለመቻል አስቆጥራለች። ምትኬ ብርሃኑ የሲዳማ ቡናን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ውጤቱን ተከትሎ መቻል በሰባት ነጥብ ሶስተኛ፣ ሲዳማ ቡና በአምስት ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከይርጋጨፌ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ
Nov 4, 2025 104
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 25/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አራተኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት አርባምንጭ ከተማ ከአዳማ ከተማ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። አንድ ጊዜ ሲሸነፍ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በሁለት ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው ሶስት ጨዋታዎች በተመሳሳይ ያለ ግብ አቻ በመለያየት በሶስት ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች በሊጉ የመጀመሪያ ድላቸውን ለማግኘት የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። የ2016 ዓ.ም የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ካደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች ሁለት ነጥብ በማግኘት 15ኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ በስድስት ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው ንግድ ባንክ የመጀመሪያ ድሉን ለማግኘት ድሬዳዋ ከተማ በሊጉ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ የሚያደርጉት ነው። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቻል ምሽት 12 ሰዓት ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሊጉ ባደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች አንድ ነጥብ ያገኘው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። መቻል በሊጉ ባደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በሰባት ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ለማሳካት ይጫወታል። መቻል ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ዳግም ይረከባል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ጨዋታውን ከይርጋጨፌ ቡና ጋር ያደርጋል
Nov 4, 2025 86
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 25/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከይርጋጨፌ ቡና ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታል። ንግድ ባንክ በካፍ ሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ተሳትፎ ምክንያት የመጀመሪያ ሶስት ሳምንታት ጨዋታዎቹን አላደረገም። ጨዋታዎቹ በተስተካካይ መርሃ ግብርነት ተይዘዋል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች ፕሪሚየር ሊግን ስምንት ጊዜ ያሸነፈ ሲሆን ያለፉት አምስት ተከታታይ የውድድር ዓመታት የዋንጫ ባለቤትም ነው። ከኢትዮጵያ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ ያደገው ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በጨዋታዎቹ ምንም ግብ አላስቆጠረም፣ ምንም ጎል አልተቆጠረበትም። በሌላኛው መርሃ ግብር መቻል ከሲዳማ ቡና ከረፋዱ አራት ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ሃዋሳ ከተማ በተመሳሳይ ዘጠኝ ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው በሊጉ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። መቻል በስድስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
በሻምፒዮንስ ሊጉ ፒኤስጂ ከባየርሙኒክ እና ሊቨርፑል ከሪያል ማድሪድ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Nov 4, 2025 107
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 25/2018 (ኢዜአ)፦ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የአራተኛ ዙር መርሃ ግብር ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ ከባየርሙኒክ ምሽት 5 ሰዓት ላይ በፓርክ ደ ፕሪንስ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ የዓለምን ትኩረት ስቧል። ፒኤስጂ እና ባየርሙኒክ ዘንድሮ ባደረጓቸው ሶስት የሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታዎች በተመሳሳይ ዘጠኝ ነጥብ በማግኘት በግብ ክፍያ ተበላልጠው አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። ሁለቱ ቡድኖች በአውሮፓ መድረክ ሲገናኙ ለ15ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 14 ጨዋታዎች ፒኤስጂ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ ሙኒክ ስድስት ጊዜ ድል ቀንቶታል። ቡድኖች እ.አ.አ በ2019/20 በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ፍጻሜ ተገናኝተው ባየር ሙኒክ 1 ለ 0 ያሸነፈበት አጋጣሚ በእርስ በእርስ ግንኙነታቸው ውስጥ በዋናነት የሚጠቀስ ነው። በውድድር ዓመቱ ያደረጋቸውን 15 ጨዋታዎች ያሸነፈው ባየር ሙኒክ ዛሬ ከፒኤስጂ ጥልቅ ፈተና ይጠብቀዋል። የጀርመኑ ቡድን የስድስት ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ነው። የ43 ዓመቱ ጣልያናዊ ዳኛ ማውሪዚዮ ማሪያኒ ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። ምሽት 5 ሰዓት ላይ በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ሊቨርፑል ከሪያል ማድሪድ የሚያደርጉት ጨዋታም ተጠባቂ ነው። በሻምፒዮንስ ሊጉ በስድስት ነጥብ 10ኛ፣ ሪያል ማድሪድ በዘጠኝ ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። ሁለቱ ቡድኖች ከዚህ ቀደም በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ 12 ጊዜ ተገናኝተው ሊቨርፑል ሰባት ጊዜ ሲያሸንፍ ሪያል ማድሪድ አራት ጊዜ አሸንፏል። አንድ ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። ቡድኖቹ በሶስት ፍጻሜዎች ላይ ተገናኝተው ሪያል ማድሪድ ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ ሊቨርፑል አንድ ጊዜ ድል ቀንቶታል። ባለፈው የውድድር ዓመት በሻምፒዮንስ ሊጉ ተገናኝተው ሊቨርፑል 2 ለ 0 ማሸነፉ አይዘነጋም። ሊቨርፑል የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫን ስድስት ጊዜ ሲያነሳ ማድሪድ 15 ጊዜ በማሸነፍ የውድድሩ ስኬታማ ክለብ ነው። በክረምቱ የዝውውር መስኮት ከሊቨርፑል ወደ ሪያል ማድሪድ በነጻ ዝውውር ያመራው ትሬንት አሌክሳንደር አርኖልድ የቀድሞ ክለቡን ለመግጠም ወደ መርሲሳይድ አምርቷል። የ41 ዓመቱ ሮማኒያዊ ስቴቫን ኮቫክስ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ጁቬንቱስ ከስፖርቲንግ ሊዝበን፣ ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከኤፍሲ ኮፐንሃገን፣ አትሌቲኮ ማድሪድ ከዩኒየን ሴንት ጂሎይስ፣ ኦሎምፒያኮስ ፒኤስቪ አይንድሆቨን እና ቦዶ ግሊምት ከሞናኮ በተመሳሳይ ከምሽቱ 5 ሰዓት ላይ ጨዋታቻውን ያደርጋሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ላይ ስላቪያ ፕራግ ከአርሰናል እና ናፖሊ ከኢንትራክት ፍራንክፈርት ይጫወታሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና አዳማ ከተማ ድል ቀንቷቸዋል
Nov 3, 2025 128
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 24/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተደርገዋል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ድሬዳዋ ከተማን 3 ለ 0 አሸንፏል። ዳግማዊት ሰለሞን ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርታለች። በሌላኛው ጨዋታ አዳማ ከተማ በነፃነት መና ግብ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 ማሸነፍ ችሏል። የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ከታንዛንያ ጋር በነበረው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ ምክንያት ተቋርጦ የነበረው የሊጉ ውድድር ትናንት መጀመሩ ይታወቃል። ትናንት በተደረጉ ጨዋታዎች ሃዋሳ ከተማ አዲስ አበባ ከተማን እና ሸገር ከተማ ባህር ዳር ከተማን በተመሳሳይ 2 ለ 0 ሲያሸንፉ ቦሌ ክፍለ ከተማ ከልደታ ክፍለ ከተማ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። የአራተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ነገ ይጠናቀቃል።
በፕሪሚየር ሊጉ ሸገር ከተማ እና ሃዋሳ ከተማ ድል ቀንቷቸዋል
Nov 3, 2025 129
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 24/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተካሄደዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን በያሬድ መኮንን ግብ 1 ለ 0 አሸንፏል። ውጤቱን ተከትሎ ሸገር ከተማ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ሲያስመዘግብ ቅዱስ ጊዮርጊስ በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናግዷል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ መቀሌ 70 እንደርታን 3 ለ 1 ረቷል። ጌታነህ ከበደ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ያሬድ ብሩክ ቀሪዋን ጎል ለሃዋሳ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሱሌይማን ሃሚድ ለመቀሌ 70 እንደርታ ብቸኛዋን ጎል ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ ሶስተኛ ድሉን ሲያስመዘግብ በተቃራኒው መቀሌ 70 እንደርታ ሶስተኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል። ዛሬ አስቀድሞ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን ሀዲያ ሆሳዕናን 2 ለ 1 አሸንፏል።