ስፖርት
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬም ቀጥለው ይካሄዳሉ
Jun 3, 2023 27
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ) ፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር የሶስተኛ ቀን ውሎ ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋሉ። በመርሃ ግብሩም ኢትዮጵያ መድን ከኢትዮጵያ ቡና ከቀኑ 7 ሰአት ላይ ይጫወታሉ። በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ኢትዮጵያ መድን በ45 ነጥብ 3ኛ ሲሆን ኢትዮጵያ ቡና በ38 ነጥብ 4ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ኢትዮጵያ መድን በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በሁለቱ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና በአንጻሩ ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሁለቱን ሲያሸንፍ በአንዱ ተሸንፏል። ሁለት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያ ዙር ባደረጉት ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን 1 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው የ27ኛ ሳምንት የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ-ግብር ወልቂጤ ከተማ ከፋሲል ከነማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በደረጃ ሰንጠረዡ ወልቂጤ ከተማ በ32 ነጥብ 13ኛ ደረጃን የያዘ ሲሆን ፋሲል ከነማ በ37 ነጥብ 6ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ወልቂጤ ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በሁለቱ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ በበኩሉ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ ሽንፈት ገጥሞታል። አንድ ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቶ ወጥቷል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ያደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ በአቻ ውጤት መጠናቀቁ የሚታወስ ነው። በተያያዘም ትናንት በተደረጉ የ27ኛ ሳምንት የሊጉ ጨዋታዎች ሃዋሳ ከተማ ወላይታ ድቻን 3 ለ 1 እንዲሁም አዳማ ከተማ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፈዋል።
በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ
Jun 2, 2023 56
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር የሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋሉ። በመርሐ-ግብሩ መሰረት ሃዋሳ ከተማ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 7 ሰአት ላይ ይጫወታሉ። በደረጃ ሰንጠረዡ ሃዋሳ ከተማ በ35 ነጥብ 8ኛ ላይ የተቀመጠ ሲሆን ወላይታ ድቻ በአንጻሩ በ33 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሃዋሳ ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ ከ19ኛ ሳምንት በኋላ ባሉ ሰባት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲሸነፍ አራት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። ተጋጣሚው ወላይታ ድቻ በአንጻሩ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው፤ በሶስቱ አቻ ሲወጣ በአንዱ ተሸንፏል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር 11ኛ ሳምንት ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። ሌላኛው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ድሬዳዋ ከተማ እና አዳማ ከተማን ከቀኑ 10 ሰአት ላይ ያገናኛል። ድሬዳዋ ከተማ በ36 ነጥብ 7ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ሲሆን አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ በሁለቱ ተሸንፏል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ ደግሞ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም፤ በሶስቱ ነጥብ ሲጋራ ሁለት ጊዜ ደግሞ ተሸንፏል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር በ13ኛ ሳምንት ባደረጉት ጨዋታ አዳማ ከተማ 2 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በተያያዘም ትናንት በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች የሊጉ መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስ ለገጣፎ ለገዳዲን 2 ለ 1 ሲያሸንፍ ሲዳማ ቡና ከአርባ ምንጭ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዛሬ ይጀመራል 
Jun 1, 2023 88
አዲስ አበባ ግንቦት 24/2015 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ሁለት ጨዋታዎች በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋሉ። በመርሃ ግብሩ ሲዳማ ቡና ከአርባ ምንጭ ከተማ ከቀኑ 7 ሰአት ላይ ይጫወታሉ። በደረጃ ሰንጠረዡ ሲዳማ ቡና በ34 ነጥብ 10ኛ ደረጃን የያዘ ሲሆን አርባ ምንጭ ከተማ በ29 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሲዳማ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች አራቱን ሲያሸንፍ በአንዱ አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው አርባ ምንጭ ከተማ በአንጻሩ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ በአራቱ ነጥብ ተጋርቷል። ጨዋታው ሲዳማ ቡና ከወራጅ ቀጠና ስጋት ለመራቅ እንዲሁም አርባ ምንጭ ከተማ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት የሚያደርጉት ጨዋታ መሆኑ ተጠባቂ ያደርገዋል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያ ዙር ያደረጉት ጨዋታ ሶስት እኩል በሆነ ውጤት መጠናቀቁ ይታወሳል። በሌላኛው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ -ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስ ከለገጣፎ ለገዳዲ ከቀኑ 10 ሰአት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በደረጃ ሰንጠረዡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ55 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ የተቀመጠ ሲሆን ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱን ያረጋገጠው ለገጣፎ ለገዳዲ በ15 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሶስቱ አሸንፎ በአንዱ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው ለገጣፎ ለገዳዲ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ሲሆን በሶስቱ ተሸንፏል በአንዱ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ካሸነፈ ከተከታዩ ባህር ዳር ከተማ ጋር ያለውን ልዩነት ወደ ስምንት ከፍ ያደርጋል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ 4 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር እስከ ግንቦት 27/ 2015 ይቆያል። የፕሪሚየር ሊጉ የውድድር እና ስነ ስርዓት ኮሚቴ በሃዋሳ ከተማ አመሻሽ ላይ በሚጥለው ከባድ ዝናብ ምክንያት የ27ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ላይ የሰዓት ማስተካከያ በማድረግ በ9 ሰዓት እንዲጀምሩ ፕሮግራም የወጣላቸው ጨዋታዎች በሙሉ 7 ሰዓት እንዲሁም በ12 ሰዓት ይጀምሩ የነበሩ ጨዋታዎች ደግሞ 10 ሰዓት ላይ እንዲጀመሩ ውሳኔ ማሳለፉ ይታወቃል። በተጨማሪም ተጀምሮ በዝናብ ምክንያት የተቋረጠ ጨዋታ ካለ በማግስቱ ከጠዋቱ 4 ሰዓት ጀምሮ በሃዋሳ አርተፊሻል ሜዳ ላይ እንደሚጠናቀቅም ገልጿል።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ከጎፈሬ የስፖርት ትጥቅ አምራች ድርጅት ጋር ስምምነት ተፈራረመ
May 31, 2023 84
አዲስ አበባ ግንቦት 23/2015 (ኢዜአ) የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ሀገር በቀል የስፖርት ትጥቅ አምራች ከሆነው ጎፈሬ ድርጅቱ ጋር ስምምነት ተፈራርሟል፡፡ በስምምነቱ መሰረት ኩባንያው በሁሉም እድሜ እርከን ለሚመረጡ የብሄራዊ ቡድን ተጫዋቾች የስፖርት ትጥቅ ያቀርባል።   የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ባህሩ ጥላሁን ስምምነቱ ለአራት ወራት የሚቆይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ትጥቁ ለገበያ ከሚቀርብበት ዋጋ 50 በመቶ ቅናሽ እንደሚያገኝ አስታውቀዋል። የጎፈሬ የስፖርት ትጥቅ አምራች ድርጅት ባለቤት አቶ ሳሙኤል መኮንን ኩባንያቸው ከዚህ በፊት ከ17 ዓመት በታች ለሆኑ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እና ለዋናው ብሄራዊ ቡድኑ የስፖርት ትጥቅ ሲያቀርብ እንደነበረ አስታውሰዋል። ይህን ተከትሎ አሁን ላይ ለዋናው ብሄራዊ ቡድን የስፖርት ትጥቅ ለማቅረብ ስምምነት በማድረጋቸው ኩራት እንደተሰማቸው ገልጸዋል ። በስምምነቱ መሰረት ኩባንያው በአፍሪካ ዋንጫ የማጣሪያ ውድድር ተሳትፎ እያደረገ ለሚገኘው ዋናው ብሄራዊ ትጥቅ ያቀርባል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም ብሄራዊ ቡድኑ በመጪው ሰኔ ወደ አሜሪካ በማቅናት ለሚያደርገው የወዳጅነት ጨዋታ የጎፈሬ ምርቶችን እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል ። ጎፈሬ የምርቱን ጥራት በማሻሻል አሁን ላይ ከሀገር ውስጥ ባለፈ ከተለያዩ የውጭ ክለቦች ጋር ስምምነት በማድረግ የስፖርት ትጥቅ እያቀረበ እንደሆነ ገልጸዋል ። በስምምነቱ መሰረት ኩባንያው ለብሄራዊ ቡድኑ ጨዋታና የመለማመጃ የስፖርት ትጥቆችን ያቀርባል ።    
የስፖርት ክለቦች የራሳቸውን ገቢ እንዲያሳድጉና ለሀገር ልማት በጎ ሚና እንዲጫወቱ በጥናትና ምርምር ማገዝ ይገባል--የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ
May 30, 2023 68
አዲስ አበባ ግንቦት 22/ 2015 (ኢዜአ) የስፖርት ክለቦች የራሳቸውን ገቢ እንዲያሳድጉና ለሀገር ልማት በጎ ሚና እንዲጫወቱ በጥናትና ምርምር ማገዝ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ጥሪ አቀረበ። የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ስምንተኛውን ዓመታዊ የስፖርት ጥናትና ምርምር ጉባዔ ዛሬ ማካሄድ ጀምሯል። የአካዳሚው የጥናትና ምርምር ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አመንሲሳ ከበደ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ስፖርት ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ትልቅ አበርክቶ አለው። በጉባዔው የስፖርት ዘርፍ ለሀገር ኢኮኖሚ ልማት ያለው አበርክቶ፣ በአትሌቲክስ ግንባታና አስተዳደር እንዲሁም የስፖርት ሕክምና ነክ ጉዳዮች የሚመለከቱ ጥናቶች መቅረባቸውን ተናግረዋል። በስፖርቱ መስክ ከሚንቀሳቀሱ ክለቦች መካከል በገቢ ራሳቸውን ባለመቻላቸው ምክንያት ደመወዝ ካለመክፈል እስከ መፍረስ የደረሱ መኖራቸውን በመጥቀስ፤ ይህን ችግር ለመቅረፍ በምርምር የተደገፉ መፍትሔዎች ለክለቦችና ለዘርፉ ባለድርሻ አካላት እንደሚቀርቡ ጠቁመዋል። ክለቦች የገቢ አቅማቸውን ለማሳደግ ከጥገኝነት የተላቀቀና ትርፋማ የገቢ አማራጭን እንዲከተሉ ማድረግ የግድ መሆኑን አንስተዋል። የስፖርት ጥናትና ምርምሮች የአመላከከት ለውጥ ለማምጣትና የስፖርቱ ተቋማት የገቢ አማራጮችን በማስፋት ለሀገር ኢኮኖሚ ልማት በጎ ሚና እንዲኖራቸው ስለሚያደርጉ ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል ብለዋል። ለዚህም በዓለም አቀፍ ደረጃ ስኬታማ ተሞክሮዎችን ቀምሮ ከሀገራዊ አውዱ አንጻር በመተንተን ምክረ ሀሳቦችን ማመላከትና ለተግባራዊነቱ መስራት እንደሚገባ ነው ያብራሩት። የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚም እንደ ተቋም የስፖርቱን ዘርፍ ለማሳደግና የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ በጥናትና ምርምር መስክ በስፋት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዘርፉ ላይ ለሚደረጉ ምርምሮች ትኩረት እየሰጡ መምጣታቸውን ጠቅሰው፤ ይህም ተጠናክሮ መጠቀል እንዳለበት ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ የስፖርት ጆርናል ድረ-ገጽ በይፋ አስመረቀ
May 30, 2023 69
አዲስ አበባ ግንቦት 22/2015 (ኢዜአ) የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ በዘርፉ የሚካሄዱ የጥናትና ምርምር ስራዎችን ተደራሽ የሚያደርግ የስፖርት ጆርናል ድረ -ገጽ በይፋ አስመረቀ፡፡ አካዳሚው ድረ- ገጹን ይፋ ያደረገው ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ቀናት የሚቆየው 8ተኛው ሀገር አቀፍ የስፖርት ምርምር ጉባኤ ላይ ነው። የአካዳሚው የጥናትና ምርምር ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አመንሲሳ ከበደ፤ድረ-ገጹ የሀገሪቱ የስፖርት ተመራማሪዎች የምርምር ሥራቸውን ለማቅረብ እንዲችሉ እድሉን የሚያመቻች ነው ብለዋል። በዋናነትም በዘርፉ የሚካሔዱ ጥናትና ምርምሮችን ለሁሉም አካላት ተደራሽ ለማድረግ ያግዛል ብለዋል። በድረ ገጹ ላይ ከሀገር ውስጥም ሆነ ሌሎች አካላት ተቀድተው ወይም ቀጥታ ተገልብጠው የመጡ ጥናቶችን ለመለየት የሚያስችል መተግበሪያ የያዘ መሆኑንም አስረድተዋል። ይኸም በአብዛኛው የሚቀርቡ ጥናቶች መደርደሪያ ላይ ከመታየት ባለፈ ተደጋጋሚነት ያላቸው በመሆኑም ይሕንኑ ለማጣራትና አዳዲስ ምርምሮችን እንዲካሔዱ ለማድረግ የሚያበረታታ ነው ብለዋል።   ድረገጹ ሀገር በቀል ዕውቀቶች እንዲሰፉና ሳይንሳዊ ይዘት እንዲኖራቸው ከማድረግ ባለፈ የሀገሪቱን ስፖርት በጥናትና ምርምር ለማሳደግ ፋይዳው የጎላ እንደሆነም ገልፀዋል። በተጨማሪም የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ የጥናትና ምርምር ሥራዎችን ለመሥራት የሚጠቅሙ የስፖርት ምርምር ቤተ ሙኩራ አጠቃቀም የልኬት መመሪያ ማዘጋጀቱን ገልፀዋል። በዚህም አካላዊ ልኬት፣ የልብ ሥርዓት ኡደት ልኬት፣ የደም ናሙና ልኬት፣ የብቃት ልኬት፣ የሥነ-ልቦና ልኬት፣ የብቃት አመልካች ልኬቶችና የብሔራዊ ቡድኖች አባላት የቅድመ ምርመራ አገልግሎቶችን እየሰጠ ነው ብለዋል።      
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 26ኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ
May 29, 2023 98
አዲስ አበባ ግንቦት 21/2015(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋሉ። በመርሐ-ግብሩ መሰረት ኢትዮጵያ መድን ከወልቂጤ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰአት ላይ ይጫወታሉ። በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ኢትዮጵያ መድን በ45 ነጥብ 3ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ሲሆን ወልቂጤ ከተማ በ29 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኢትዮጵያ መድን በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ የሊጉ ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በአንዱ ተሸንፎ በሁለቱ አቻ ወጥቷል። በአንጻሩ ወልቂጤ ከተማ ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሁለት ጊዜ ተሸንፎ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያ ዙር ያደረጉት ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በ26ኛ ሳምንት የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ-ግብር የመጨረሻው ጨዋታ በሀዲያ ሆሳዕና እና ኢትዮጵያ ቡና መካከል ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይደረጋል። ሀዲያ ሆሳዕና በ36 ነጥብ 5ኛ ደረጃን የያዘ ሲሆን ኢትዮጵያ ቡና በ35 ነጥብ 7ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሀዲያ ሆሳዕና ካለፉት አምስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በአንዱ ተሸንፎ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። ሁለት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ያደረጉት ጨዋታ ሀዲያ ሆሳዕና 1 ለ 0 ማሸነፉ ይታወሳል። ትናንት የሲዳማ ቡና እና ወላይታ ድቻ ጨዋታ እስከ እረፍት ያለምንም ግብ የተጠናቀቀ ቢሆንም በሃዋሳ በጣለው ከባድ ዝናብ ሜዳው ማጫወት እንደማይችል የጨዋታ አመራሮች በማረጋገጣቸው መቋረጡ ይታወቃል። ከዛሬ ሁለቱ ጨዋታዎች ቀደም ብሎ ጨዋታው ከቆመበት ደቂቃ(ሁለተኛው አጋማሽ) በሃዋሳ ዩንቨርሲቲ ስታዲየም ከቀኑ 7 ሰዓት እንደሚደረግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አክሲዮን ማህበር አመልክቷል። በሌላ በኩል ትናንት በተደረገ የ26ኛ ሳምንት ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ ፋሲል ከነማን 2 ለ 1 አሸንፏል።
በፕሪሚየር ሊጉ የ26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ
May 27, 2023 147
አዲስ አበባ ግንቦት 19/2015 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋሉ። መቻል ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰአት ላይ ይጫወታሉ። በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ መቻል በ33 ነጥብ 9ኛ ሲሆን ሃዋሳ ከተማ በ34 ነጥብ 7ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። መቻል በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በሁለቱ ተሸንፎ በአንዱ አቻ ወጥቷል። ሃዋሳ ከተማ በበኩሉ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ሁለት ጊዜ ተሸንፎ በሶስቱ ነጥብ ተጋርቷል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ጨዋታ መቻል 2 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ሌላኛው የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት ጨዋታ አርባ ምንጭ ከተማን እና ኢትዮ ኤሌክትሪክን ከምሽቱ 12 ሰአት ላይ ያገናኛል። አርባ ምንጭ ከተማ በ26 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኝ ሲሆን ቀድሞ ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱን ያረጋገጠው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ12 ነጥብ የመጨረሻውን 16ኛ ደረጃ ይዟል። አርባ ምንጭ ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በአንዱ ሲሸነፍ በአራቱ ነጥብ ተጋርቷል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ባለፉት አምስት ጨዋታዎች በሶስቱ ሽንፈት የገጠመው ሲሆን ሁለት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። አርባ ምንጭ ከተማ የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፈ ወልቂጤ ከተማ ጨዋታውን እስኪያደርግ ከወራጅ ቀጠና የመውጣት እድል ያገኛል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ያደረጉት ጨዋታ ሁለት አቻ በሆነ ውጤት መጠናቀቁ የሚታወስ ነው። በተያያዘ ዜና ትናንት በተደረገ የ26ኛ ሳምንት ጨዋታ ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱን ያረጋገጠው ለገጣፎ ለገዳዲ አዳማ ከተማን 1 ለ 0 በማሸነፍ በሊጉ ሶስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። ተጠባቂው የቅዱስ ጊዮርጊስ እና ባህር ዳር ከተማ ጨዋታ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በጣለው ከባድ ዝናብ ምክንያት ሜዳው ማጫወት ባለመቻሉ ላልተወሰነ ጊዜ እንዲራዘም መደረጉ ይታወቃል።
የዋንጫ ተፎካካሪዎቹ ቅዱስ ጊዮርጊስና ባህር ዳር ከተማ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
May 26, 2023 147
አዲስ አበባ ግንቦት 18/2015 (ኢዜአ):-በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር የፕሪሚየር ሊጉ መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ተከታዩ ባህር ዳር ከተማ የሚያደርጉት ጨዋታ በእግር ኳስ አፍቃሪው ዘንድ በጉጉት ይጠበቃል። በሊጉ የዋንጫ ፉክክር ወሳኝ የሆነው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 12 ሰአት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋል። በደረጃ ሰንጠረዡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ55 ነጥብ 1ኛ ሲሆን ባህር ዳር ከተማ በ50 ነጥብ 2ኛ ደረጃን ይዟል። በአሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ የሚሰለጥነው ቅዱስ ጊዮርጊስ እስከ አሁን በፕሪሚየር ሊጉ ካደረጋቸው 25 ጨዋታዎች 16ቱን ሲያሸንፍ 2 ጊዜ ተሸንፏል፤ 7 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በ25ቱ ጨዋታዎች ፈረሰኞቹ 46 ግብ ሲያስቆጥሩ 16 ጎሎችን አስተናግደዋል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለፉት አምስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች በሶስቱ አሸንፎ በአንድ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በአሰልጣኝ ደግ አረገ ይግዛው የሚመራው ባህር ዳር ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 25 ጨዋታዎች 14ቱን ሲያሸንፍ በሶስቱ ተሸንፏል፤ 8 ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል።   የጣና ሞገዶቹ በ25ቱ ጨዋታዎች 44 ጎሎችን ሲያስቆጥሩ 22 ግቦችን አስተናግደዋል። ባህር ዳር ከተማ ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሁለቱን አሸንፎ ሁለቱን ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቅዱስ ጊዮርጊስ የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፈ ከተከታዩ ባህር ዳር ከተማ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ስምንት ከፍ በማድረግ 16ኛውን የፕሪሚየር ሊጉ ዋንጫ ለማንሳት ይበልጥ ይቀርባል። በአንጻሩ ባህር ዳር ከተማ በዋንጫ ፉክክሩ ለመቆየት የዛሬውን ጨዋታ ማሸነፍ የሚጠበቅበት ሲሆን ጨዋታውን ካሸነፈ ከፈረሰኞቹ ጋር ያላቸውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ ያደርጋሉ። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያ ዙር በ10ኛ ሳምንት በድሬዳዋ ስታዲየም ያደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ በአቻ ውጤት መጠናቀቁ የሚታወስ ነው። ከሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ቀደም ብሎ የ26ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱን ባረጋገጠው ለገጣፎ ለገዳዲ እና አዳማ ከተማ መካከል ከቀኑ ዘጠኝ ሰአት ላይ ይደረጋል። በደረጃ ሰንጠረዡ ለገጣፎ ለገዳዲ በ12 ነጥብ 16ኛ ደረጃን የያዘ ሲሆን አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ 8ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያ ዙር ባደረጉት ጨዋታ አዳማ ከተማ 3 ለ 0 ማሸነፉ ይታወሳል። የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ26ኛ ሳምንት መርሐ- ግብር እስከ ግንቦት 21/ 2015 ዓ.ም ይቆያል።
በመጪው መስከረም በፊንላንድ በሚካሄደው ኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ሻምፒዮና ኢትዮጵያን የሚወክሉ ስምንት ስፖርተኞች ይሳተፋሉ
May 24, 2023 198
አዲስ አበባ ግንቦት 16/2015(ኢዜአ)፡-በመጪው መስከረም በፊንላንድ ታምፔሬ በሚካሄደው ኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ሻምፒዮና ኢትዮጵያን ወክለው ስምንት ስፖርተኞች እንደሚሳተፉ የኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ቴኳንዶ አሶሴሽን አስታወቀ፡፡ የኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ቴኳንዶ አሶሴሽን ፕሬዝዳንት ኢንስትራክተር ጌታቸው ሺፈራው ለኢዜአ እንደገለጹት ኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ስፖርት በኢትዮጵያ መዘውተር የጀመረው ከ1980ዎቹ ወዲህ መሆኑን ይናገራሉ። ስፖርቱ በወቅቱ ከኮሪያ ሀገር ልምድ በቀሰሙ የፖሊስ ሰራዊት አባላት እንደተጀመረ አስታውሰው ፤በጊዜ ሂደት ስፖርቱ ከፖሊስ አባላት ውጭ በሌላው የማህበረሰብ አባላት እየተዘወተረና እየተስፋፋ እንደመጣ ተናግረዋል። አሁን ላይ በኢትዮጵያ ከ250 በላይ ኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ስፖርት ክለባት መኖራቸውንና በእያንዳንዱ ክለብ ከ25 እስከ 30 ሰልጣኞች እንደሚሳተፉም ነው የገለጹት፡፡ ስፖርቱ ጤናማ አካልን በማጎናጸፍ ፣ጤናን በመጠበቅና ማህበራዊ ግንኙነትን ማጎልበትን ጨምሮ በርካታ ጥቅሞች እንዳሉት ነው የተናገሩት። በተጨማሪ ስፖርቱ ዓለም አቀፍ ውድድር ስፖርት እንደመሆኑ መጠን አሶሴሽኑ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ስፖርተኞችን እንደሚያሳትፍ ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከተሳተፈችባቸው የተለያዩ ውድድሮች መካከል ከሶስት ዓመት በፊት በአፍሪካ ደረጃ በታንዛኒያ በተደረገ ውድድር የአንደኝነት ደረጃ ይዛ ማጠናቀቋን አስታውሰዋል። በመጪው ዓመት መስከረም ወር በፊንላንድ ቴምፔሬ በሚካሄደው ኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ ተሳታፊ እንደምትሆን ገልጸዋል። በውድድሩ የሚካፈሉ የብሔራዊ ቡድን አባላት ምርጫ በሚያዚያ ወር በአዲስ አበባ በተካሄደው ሀገር አቀፍ የክለቦች ሻምፒዮና መካሄዱንም አብራርተዋል፡፡ በዚህም ስምንት ተወዳዳሪዎች መመረጣቸውን ጠቅሰው፤ ከሚቀጥለው ሳምንት በኋላ ልምምድ እንደሚጀምሩ ተናግረዋል፡፡ በኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ስፖርት በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የማስተር ማዕረግ ያገኙት ማስተር ወጋየሁ በሃይሉ ከብሔራዊ ቡድኑ አሰልጣኛች መካከል አንዱ ሲሆኑ፤ ቡድኑ ጠንካራ ተወዳዳሪ እንዲሆን የሚያስችሉ ስራዎች እንደሚያከናውኑ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በኢንተርናሽናል ቴኳንዶ ስፖርት 60 ኢንስትራክተሮችና አንድ ማስተርነት ደረጃ የደረሰ ባለሙያዎች እንዳሏት ጠቅሰው፤ ይህም ከአፍሪካ የተሻሉ ባለሙያዎች እንዲኖራት ማድረጉን ተናግረዋል በሻምፒዮናው መሳተፍ ልምድና ተሞክሮ ለመቅሰምና ስፖርቱን የበለጠ ለማሳደግ የሚኖረው ሚና ከፍተኛ መሆኑን በማስታወስ ፤ብሔራዊ ቡድኑ ውጤታማ እንዲሆን አጋር አካላት የሚጠበቅባቸውን ትብብር እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡                            
የአፍሪካ ሪጂን 4 ጎልፍ ሻምፒዮና በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት አዲስ አበባ ሊካሄድ ነው
May 23, 2023 160
አዲስ አበባ ግንቦት 15/2015(ኢዜአ):- የአፍሪካ ሪጂን 4 ጎልፍ ሻምፒዮና በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ጎልፍ ክለብ አሶሴሽን ገለጸ። አሶሴሽኑ ውድድሩን ለማካሄድ እየተደረገ ያለውን ዝግጅት አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል። የኢትዮጵያ ጎልፍ ክለብ አሶሴሽን ፕሬዝዳንት ተሾመ ሞሲሳ የሻምፒዮናው ውድድር ከግንቦት 28 እስከ ሰኔ 4 ቀን 2015 ዓ.ም በአዲስ አበባ ጎልፍ ክለብ ይካሄዳል ብለዋል። በውድድሩ ከአፍሪካ ሪጅን 4 አባል አገራት መካከል አምስት የውጭ አገራት በውድድሩ ለመሳተፍ ማረጋገጫ መስጠታቸውን ነው የተናገሩት። በአሁኑ ወቅት ውድድሩን ለማዘጋጀት አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን በመጠቆም። በውድድሩ ኢትዮጵያም ተካፋይ እንደመሆኗ ስፖርተኞች ተመርጠው ዝግጅት እያደረጉ ነው ብለዋል። ውድድሩ በኢትዮጵያ መካሄዱ ለአገር ገጽታ ግንባታና የእርስ በእርስ ግንኙነት መጠናከር ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ነው የገለፁት። የጎልፍ ስፖርት በኢትዮጵያ የተጀመረው በቀዳማዊ ሃይለሥላሴ ዘመን ቢሆንም ስፖርቱ በሚፈለገው ደረጃ ሳያድግ ቆይቷል። ያም ሆኖ ከ1990 ዓ.ም ጀምሮ ስፖርቱ የተሻለ የሚባል እንቅስቃሴ እየታየበት የመጣ ሲሆን ኢትዮጵያ 2008 ዓ.ም በታሪኳ የመጀመሪያ የሆነ የምስራቅ አፍሪካ ጎልፍ ውድድር አዘጋጅታ እንደነበር መረጃዎች ያሳያሉ።  
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ
May 23, 2023 168
አዲስ አበባ ግንቦት 15/2015(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋሉ። በመርሐ-ግብሩ መሰረት ሃዋሳ ከተማ ከኢትዮጵያ መድን ከቀኑ ዘጠኝ ሰአት ላይ ይጫወታሉ። በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ሃዋሳ ከተማ በ33 ነጥብ 8ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ሲሆን ኢትዮጵያ መድን በ44 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ሃዋሳ ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ሁለት ጊዜ ተሸንፏል በሶስቱ አቻ ወጥቷል። በአንጻሩ ኢትዮጵያ መድን ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሁለቱን አሸንፎ በሁለቱ ተሸንፎ አንድ ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያ ዙር ያደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ በአቻ ውጤት መጠናቀቁ የሚታወስ ነው። ሌላኛው የ25ኛ ሳምንት የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ-ግብር የመጨረሻው ጨዋታ በኢትዮ ኤሌክትሪክና መቻል መካከል ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይደረጋል። ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ በ11 ነጥብ የመጨረሻውን 16ኛ ደረጃ ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። መቻል በአንጻሩ በ32 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ ባለፉት አምስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። በአራቱ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው መቻል በበኩሉ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በዛሬው ጨዋታ ከተሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱን የሚያረጋግጥ ሁለተኛ ክለብ ይሆናል። ለገጣፎ ለገዳዲ ከቀናት በፊት ከፕሪሚየር ሊጉ መውረዱ የሚታወስ ነው። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት መጠናቀቁ ይታወቃል። በተያያዘም ትናንት በተደረጉ የ25ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ሲዳማ ቡና ፋሲል ከነማን 1 ለ 0 እንዲሁም ድሬዳዋ ከተማ ወልቂጤ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፈዋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬም ቀጥለው ይካሄዳሉ
May 22, 2023 155
አዲስ አበባ ግንቦት 14/2015 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር የሶስተኛ ቀን ውሎ ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋሉ። ፋሲል ከነማ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ ዘጠኝ ሰአት ላይ ይጫወታሉ። በሊጉ የደረጃ ሰንጠረዥ ፋሲል ከነማ በ37 ነጥብ 5ኛ ሲሆን ሲዳማ ቡና በ30 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ፋሲል ከነማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች ሶስቱን አሸንፎ በአንዱ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በአንጻሩ ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ በሁለቱ ተሸንፏል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያ ዙር ባደረጉት ጨዋታ ፋሲል ከነማ 4 ለ 2 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው የ25ኛ ሳምንት የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ-ግብር ወልቂጤ ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወልቂጤ ከተማ በ29 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሲሆን ድሬዳዋ ከተማ በ30 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ወልቂጤ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በአንዱ ተሸንፎ ሁለት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ በሶስቱ ተሸንፏል። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ያደረጉት ጨዋታ ሁለት አቻ በሆነ ውጤት መጠናቀቁ ይታወሳል። በተያያዘም ትናንት በተደረጉ የ25ኛ ሳምንት የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሀዲያ ሆሳዕና ባህር ዳር ከተማን እንዲሁም የሊጉ መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወላይታ ድቻን በተመሳሳይ 2 ለ 1 አሸንፈዋል።
52ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተጠናቀቀ
May 21, 2023 155
አዲስ አበባ ግንቦት 13/2015(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አዘጋጅነት ሲካሄድ የቆየው 52ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተጠናቀቀ። በ52ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ የተሳተፉና አሸናፊ የሆኑ ክለቦች ከዕለቱ የክብር እንግዶች ሽልማት ተቀብለዋል። በሁለቱም ፆታዎች አጠቃላይ አሸናፊ የሆኑ ቡድኖች የዋንጫና የገንዘብ ሽልማት ከእለቱ የክብር እንግዳ በባህልና ስፖርት ሚኒስትር የስፖርት ዘርፍ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት እና ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንት አትሌት ገዛኸኝ አበራ እጅ ተረክበዋል። እንዲሁም ለሻምፒዮናው መሳካት ሚና ለነበራቸው አካላት የምስጋና ምስክር ወረቀት ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ጽህፈት ቤት ተወካይ አቶ ዮሐንስ እንግዳ እጅ ተቀብለዋል። በእለቱ ሪከርድ ያሻሻሉ፣ 2 እና ከዛ በላይ ወርቅ ያስመዘገቡ አትሌቶችም የገንዘብ ማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። አጠቃላይ ውጤቱም፦ በሴቶች አሸናፊ፣ 1ኛ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ204 ነጥብ፣ 2ኛ መቻል በ170 ነጥብ፣ እንዲሁም 3ኛ ጥሩነሽ ዲባባ አትሌቲክስ ማሰልጠኛ ማዕከል በ55 ነጥብ አሸናፊ ሆነዋል። በወንዶች አሸናፊ፣ 1ኛ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ154 ነጥብ፣ 2ኛ መቻል በ125 ነጥብ እንዲሁም 3ኛ ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ 104 ነጥብ በመሰብሰብ አሸናፊ መሆናቸው ተገልጿል። ሻምፒዮናው የክልሎች እና የከተማ አስተዳደሮች ቡድኖች እና ክለቦች በሰልፍ ትርኢት በክብር እንግዶች ፊት ያለፉ ሲሆን በኢትዮጵያ ህዝብ መዝሙር በመዘመር ተጠናቋል። ሻምፒዮናው አጠቃላይ አሸናፊ፣ 1ኛ የኢትዮጵያ ንግደ ባንክ በ358 ነጥብ፣ 2ኛ መቻል በ295 ነጥብ እንዲሁም 3ኛ ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ በ158 ነጥብ አሸናፊዎች ሆነው መጠናቀቁን የፌዴሬሽኑ መረጃ ያመላክታል።
በዓለም አደባባይ አገርን ላስጠሩ የሲዳማ ክልል አትሌቶች እውቅናና ሽልማት ተሰጠ
May 21, 2023 152
ሀዋሳ ግንቦት 13/2015(ኢዜአ)፦ በአትሌቲክስ ስፖርት በዓለም አደባባይ አገርን ላስጠሩ የሲዳማ ክልል አትሌቶች የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በተገኙበት እውቅናና ሽልማት የመስጠት መርሃ-ግብር ተካሄደ። በተካሄደው መርሃ ግብር በማራቶን ውድድር ለአስር ዓመታት የዓለም ክብረ ወሰን ባስጠበቀው መቶ አለቃ አትሌት በላይነህ ዴንሳሞ የተጻፈ "የተፈተነ ጽናት" የተሰኘ መጽሐፍም ከ6 ሚሊዮን በሚበልጥ ገንዘብ ተሽጧል።   የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዴሞ በዚህ ጊዜ ባስተላለፉት መልዕክት በአትሌትክሱ ዘርፍ የአገርን ሰንደቅ ዓላማ በዓለም አደባባይ ከፍ ላደረጉ የክልሉ አትሌቶች የክልሉ ህዝብና መንግስት ትልቅ አክብሮት እንዳለው ገልጸዋል። የቀደምት አትሌቶችን ጨምሮ የተሰጠው እውቅናና ሽልማት በአትሌትክሱ ዘርፍ ያለውን የክልሉን እምቅ አቅም በአግባቡ ለመጠቀምና ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት መነሳሳት ለመፍጠር ታስቦ መሆኑን ተናግረዋል። አቶ ደስታ እንዳሉት የክልሉ መንግስት በአትሌትክስ ዘርፍ ሀገርን ሊያስጠሩ የሚችሉ ወጣቶችን ለማፍራት በትኩረት እየሰራ ነው። መቶ አለቃ አትሌት በላይነህ ዴንሳሞን እና አትሌት ቱርቦ ቱሞን ከመሳሰሉት ስመጥር አትሌቶች ወጣቱ ትውልድ አሸናፊነትና የዓላማ ጽናት መማር እንዳለበትም ገልጸዋል። በማራቶን የዓለም ክብረወሰን ያስመዘገበው መቶ አለቃ አትሌት በላይነህ ዴንሳሞም የክልሉ መንግስት በሀዋሳ ከተማ ባዘጋጀለት 1ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ አካባቢውንና ስሙን የሚያስጠራ ሥራ እንዲሰራም ጠይቀዋል።   የሲዳማ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ፍሬው አሬራ በበኩላቸው የእውቅናና የሽልማት መርሀ-ግብሩ ሦስት ዋና ዋና ዓላማዎችን ያነገበ መሆኑን ተናግረዋል። ለክልሉ ታዋቂ አትሌቶች እውቅና መስጠት፣ ተተኪ አትሌቶችን ማፍራት እና የስፖርት ልማት ሥራን ማገዝ ዓላማዎቹ መሆኑንም ገልጸዋል። በእውቅናና ሽልማት መርሀ-ግብሩ "የተፈተነ ጽናት" በሚል ርዕስ በመቶ አለቃ አትሌት በላይነህ ዴንሳሞ የተጻፈ መጽሐፍ ከ6 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ መሸጡንም ኮሚሽነር ፍሬው አስታውቀዋል።   የመጽሀፉ ሽያጭ ገንዝብ በቼክ፣ በጥሬ ገንዘብና ቃል በመግባት የተሰበሰበ መሆኑንም ጠቁመዋል። የክልሉ መንግስት በሃዋሳ ከተማ አስተዳደር ለመቶ አለቃ አትሌት በላይነህ ዴንሳሞ ያዘጋጀውን 1ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ሳይት ፕላን አዘጋጅቶ እንደሚያስረክብም አመልክተዋል። በህይወት ለሌለው አትሌት ቱርቦ ቱሞ ቤተሰቦችም 1 ሚሊዮን ብር፣ በዓለምና በአፍሪካ የአትሌትክስ ውድድሮች አሸናፊ ለሆኑ ሦስት ወጣት ተተኪ አትሌቶች ደግሞ ለእያንዳንዳቸው የ500 ሺህ ብር ሽልማት መሰጠቱን ኮሚሽነሩ ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኘው መቶ አለቃ አትሌት በላይነህ ዴንሳሞ ከረዥም ዓመታት በኋላ የክልሉ መንግስት ለሰጠው እውቅና አመስግኗል። የክልሉ መንግስት በአትሌትክሱ ዘርፍ የሚያከናውነውን ተግባር በመደገፍ ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት እንደሚሰራም ነው ያረጋገጠው። የአትሌት ቱርቦ ቱሞ ልጅ ወጣት መብራት ቱርቦ በበኩሏ አባቷ ከሞተ ከ14 ዓመት በኋላ የክልሉ መንግስት ለሰጠው እውቅናና ሽልማት አመስግናለች። የቀደሞ የዘርፉን ጀግኖች መዘከርና ማስታወስ ለወጣት አትሌቶች አቅም እንደሚፈጥርም ተናግራለች። በመድረኩ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞን ጨምሮ የተለያዩ የሥራ ሀላፊዎች፣ ባለሀብቶችና የሃገር ሽማግሌዎች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም