ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ደቡብ አፍሪካ ጥሎ ማለፉን ተቀላቀለች
Dec 29, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሁለት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ማምሻውን ተደርገዋል። በማራካሽ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ደቡብ አፍሪካ ዚምባቡዌን 3 ለ 2 አሸንፋለች። ሺፓንግ ሞሬሚ እና ላይል ፎስተር በጨዋታ፣ ኦስዊን አፖሊስ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ታዋንዳ ማስዋንሃይስ እና የደቡብ አፍሪካው ኦውብሬይ ማፖሳ ሞዲባ በራሱ ላይ ለዚምባቡዌ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ላይ ደቡብ አፍሪካ ብልጫ ወስዳ ብትጫወትም ከዚምባቡዌ ጠንካራ ፈተና ገጥሟታል። ውጤቱን ተከትሎ ደቡብ አፍሪካ በስድስት ነጥብ በምድብ ሁለት ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ለጥሎ ማለፍ ማለፏን አረጋግጣለች። ዚምባቡዌ በአንድ ነጥብ አራተኛ ደረጃን በመያዝ ከውድድሩ ውጭ ሆናለች። በተመሳሳይ በዚሁ ምድብ አንጎላ እና ግብጽ ማምሻውን በአጋዲር ስታዲየም ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። አስቀድሞ ወደ ጥሎ ማለፍ የገባችው ግብጽ በሰባት ነጥብ ምድቡን በመሪነት አጠናቃለች። በአንጻሩ አንጎላ በሁለት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች።
መቀሌ 70 እንደርታ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ነጥብ ተጋርተዋል
Dec 29, 2025 60
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አቤል ያለው በ40ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ቅዱስ ጊዮርጊስ መሪ ሆኗል። በ80ኛው ደቂቃ ተመስገን ተስፋየ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ግብ ለመቀሌ 70 እንደርታ አንድ ነጥብ አስገኝታለች። ጨዋታውን ተከትሎ መቀሌ 70 እንደርታ በስምንት ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በ18 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ዛሬ በተደረጉ የ12ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ፋሲል ከነማ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 1 ለ 0 ሲያሸንፍ ወላይታ ድቻ ከአርባምንጭ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከባህር ዳር ከተማ ያደረጓቸው ጨዋታዎች በተመሳሳይ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ባህር ዳር ከተማ አቻ ተለያዩ
Dec 29, 2025 65
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ባህር ዳር ከተማ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የወልዋሎው ተጫዋች ሱልጣን በርሄ በ34ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ባህር ዳር ከተማ በጨዋታው ላይ ያገኘውን የቁጥር ብልጫ መጠቀም አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በዘጠኝ ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውሰጥ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በ15 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። በአሁኑ ሰዓት መቀሌ 70 እንደርታ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን እያደረጉ ነው ።
ወላይታ ድቻ እና አርባምንጭ ከተማ ነጥብ ተጋሩ
Dec 29, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ወላይታ ድቻ እና አርባምንጭ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተደርጓል። ፋሲል ከነማ የሊጉ መሪ ሆነ ወንድማማቾች በአፍሪካ ዋንጫ ውጤቱን ተከትሎ ወላይታ ድቻ በ11 ነጥብ ከ17ኛ ወደ 16ኛ ደረጃውን ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። አርባምንጭ ከተማ በስድስት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው።
ወንድማማቾች በአፍሪካ ዋንጫ
Dec 29, 2025 96
የአፍሪካ ዋንጫ መልከ ብዙ ውድድር ነው። የሀገራት ተቀናቃኝነት፣ ታሪካዊ ገድሎች፣ አይረሴ የተጫዋቾች የግል ብቃት፣ ጨዋታ ወሳኝ ግቦች እና ዋንጫን ከፍ አድርጎ የማንሳት የኩራት እና የሀገር ፍቅር ስሜት መገለጫዎቹ ናቸው። ከሚቆጠሩ ግቦች እና ዋንጫዎች ባለፈ ቤተሰባዊ ገጽታ ያለው ነው። የአፍሪካ ዋንጫ በርካታ ወንድማማች ተጫዋቾች በአንድ ሀገር ማልያ ሲጫወቱ የተመለከትንባቸው አጋጣሚዎች በርካታ ናቸው። በአህጉራዊው መድረክ የ68 ዓመታት ጉዞ አብረው የተጫወቱ ወንድማቾች በዚሁ ጽሁፍ እንመለከታለን። 1. ኢታሎ እና ሉቺያኖ ቫሳሎ (ኢትዮጵያ) ኢታሎ ቫሳሎ እና ሉቺያኖ ቫሳሎ በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጫወቱ ወንድማማቾች መሆናቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1962 ባዘጋጀችው ሶስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ የቫሳሎ ወንድማማቾች አንድ ላይ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጫውተዋል። ሉቺያኖ በውድድሩ ላይ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ከግብጹ ባደዊ አብድል ፈታህ ጋር በጋራ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኖ አጠናቋል። ሉቺያኖ የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች ተብሎ የተመረጠ ሲሆን ይህም በውድድሩ ታሪክ የኮከብ ተጫዋችነትን ሽልማት ያገኘ የመጀመሪያው ተጫዋች እንዲሆን አስችሎታል። ኢትዮጵያ በወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫን ማንሳቷ የሚታወስ ነው። 2. ሆሳም እና ኢብራሂም ሀሰን (ግብጽ) ሆሳም ሀሰን እና ኢብራሂም ሀሰን በአፍሪካ ዋንጫው ስኬታማ የሚባሉ ወንድማማች ተጫዋቾች ናቸው። እ.አ.አ በ1986 ግብጽ ያስተናገደችውን 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና እ.አ.አ በ1998 በቡርኪናፋሶ የተካሄደውን 21ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ግብጽ ስታነሳ የቡድኑ አባላት ነበሩ። ወንድማማቾቹ የአፍሪካ ዋንጫን ሁለት ጊዜ በማንሳት ባለ ክብረ ወሰን ናቸው። የ59 ዓመቱ ሆሳም ሀሰን በአሁኑ ሰዓት የግብጽ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ነው። በተጫዋችነቱ በ177 ጨዋታዎች 69 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የምንጊዜውም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ነው። 3. አልበርት ባዋንጋ እና ሮበርት ካዛዲ (ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ) ሁለቱ ወንድማማቾች ግብጽ እ.አ.አ በ1974 ባዘጋጀችው ዘጠነኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። በወቅቱ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ዛምቢያን በማሸነፍ ዋንጫውን ስታነሳ የታሪካዊው ድል አካል ነበሩ። 4. አንድሬ ካና ቢይክ እና ፍራንስዋ ኦማም ቢይክ (ካሜሮን) ሁለቱ ወንድማማቾች በሶስት የአፍሪካ ውድድሮች ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። ተጨዋቾቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በአህጉራዊ መድረክ በጋራ የመሰለፍ እድል ያገኙት እ.አ.አ በ1988 በሞሮኮ አስተናጋጅነት በተካሄደው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው። እ.አ.አ በ1990 በአልጄሪያ በተካሄደው 17ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ሴኔጋል እ.አ.አ በ1992 ባዘጋጀችው 18ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። ጣልያን እ.አ.አ በ1990 ባዘጋጀችው 14ኛው የዓለም ዋንጫ ከወንድማማቾቹ ታናሹ ፍራንስዋ ኦማም ቢይክ ካሜሮን አርጀንቲናን 1 ለ 0 ባሸነፈችበት ጨዋታ ባስቆጠራት ጎል ሁሌም በሀገሬው ሰዎች ሲወሳ ይኖራል። 5. አንድሬ አየው እና ጆርዳን አየው (ጋና) ጋናውያኑ ወንድማሞች የአፍሪካ ዋንጫ ሲነሳ ሁሌም የሚታወሱ ተጫዋቾች ናቸው። በስድስት የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ አብረው ተሰልፈዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ አብረው የሰለፉት ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን እ.አ.አ በ2012 ባዘጋጁት 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። የአየው ወንድማማቾች እ.አ.አ በ2015 ኢኳቶሪያል ጊኒ ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማንሳት ተቃርበው የነበሩ ቢሆንም በፍጻሜው በኮትዲቭዋር በመለያ ምት ተሸንፈው ህልማቸው ሳይሳካ ቀርቷል። የታዋቂው አፍሪካዊ ተጫዋች አብዲ ፔሌ ልጆች የሆኑት አንድሬ እና ጆርዳን አየው እ.አ.አ በ2023 በኮትዲቭዋር አስተናጋጅነት በተካሄደው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለመጨረሻ ጊዜ በጋራ ተሰልፈዋል። ጋና እ.አ.አ በ2008 ባዘጋጀችው 26ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጋናዊው አጥቂ አሳሞሃ ጊያን እና ታናሽ ወንድሙ ባፎር አንድ ላይ ተጫውተዋል። በተጨማሪም በዛው ውድድር ላይ ጋናውያኑ ወንድማማቾች ሪቻርድ ኪንግስተን እና ላሪያ ጊንግስተን አብረው የመጫወት እድል አግኝተዋል። 6. ኮሎ ቱሬ እና ያያ ቱሬ (ኮትዲቭዋር) በአፍሪካ እግር ኳስ ውስጥ ስማቸው በግንባር ቀደምትነት ከሚነሱ ተጫዋቾች መካከል ኮሎ ቱሬ እና ያያ ቱሬ ይጠቀሳሉ። ወንድማማቾቹ ለመጀመሪያ ጊዜ አብረው የተሰለፉት እ.አ.አ በ2006 በግብጽ አስተናጋጅነት በተካሄደው 25ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በወቅቱ ኮትዲቭዋር ለፍጻሜ ደርሳ በግብጽ ተሸንፋለች። ኢኳቶሪያል ጊኒ እ.አ.አ በ2015 ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ኮትዲቭዋር ጋናን በማሸነፍ ዋንጫውን ለሁለተኛ ጊዜ ስታነሳ በጋራ የድሉ ተቋዳሽ ሆነዋል። የቱሬ ወንድማማቾች ለስድስት ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫው አብረው ተጫውተዋል። 7. የሞሪታኒያ እና ዛምቢያ ወንድማማች ተጫዋቾች እ.አ.አ በ2023 ኮትዲቭዋር ባስተናገደችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሞሪታኒያ ብሄራዊ ቡድን ስብስብ ከሁለት ቤተሰብ በተመሳሳይ ሁለት ወንድማማቾች መሳተፋቸው የተለየ ትኩረት ስቧል። ኑህ መሐመድ አብድ እና ታናሹ ሲዲ መሐመድ አህመድ አብድ በተከላካይ እና አማካይ መስመር ላይ ተሰልፈው ተጫውተዋል። ላሚን ባ እና ኤል ሃጂ ባ ለሞሪታኒያ ብሄራዊ ቡድን በመሰለፍ መጫወት ችለዋል። ዛምቢያዊያኑ ክርስቶፈር እና ፍሊክስ ካቶንጎ እ.አ.አ በ2012 ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን በጣምራ ባዘጋጁት 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዛምቢያ ኮትዲቭዋር በማሸነፍ የአፍሪካ ዋንጫን ስታነሳ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል። ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ2013 ባዘጋጀችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይም በጋራ ተሰልፈው ተጫውተዋል። ዛምቢያውያኑ ወንድማማቾች ኬኔት እና ሞርዶን ማሊቶሊ እ.አ.አ በ1994 በቱኒዚያ በተካሄደው 19ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ1996 ባዘጋጀችው 20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አንድ ላይ ተሰልፈዋል። አለን ትራኦሬ እና ኢብራሂማ ትራኦሬ (ቡርኪናፋሶ) በ30ኛው እና 31ኛው የአፍሪካ ፣ ሳምቡ ያታባሬ እና ሙስጠፋ ያታባሬ (ማሊ) በተመሳሳይ በ30ኛው እና 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ፒተር ንዶልቩ እና አዳም ንዶልቩ (ዚምባቡዌ) በ24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ሳሉ፣ ባቺሩ እና ታጁ (ቶጎ) በ22ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ቾሞጎ ኦማር እና ሴዲያት ኦማር (ቤኒን) በ24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ መሐመድ እና ሙሳ ካሎን (ሴራሊዮን) በ20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ሳሚር ሳሊሚና አዴል ሳሊሚ (ቱኒዚያ) በ19ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አብረው የተሰለፉ ተጫዋቾች ናቸው። በአፍሪካ ዋንጫ ከተሰለፉ ወንድማማቾች መካከል ስድስቱ የአፍሪካ ዋንጫን ማንሳታቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል።
ፋሲል ከነማ የሊጉ መሪ ሆነ
Dec 29, 2025 55
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ፋሲል ከነማ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 1 ለ 0 አሸንፏል። ወንድማማቾች በአፍሪካ ዋንጫ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አንዋር ሙራድ በ62ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ ስድስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ፋሲል ከነማ በ24 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከሲዳማ ቡና በጊዜያዊነት ተረክቧል። ፋሲል ከነማ በሊጉ ምንም ሽንፈት ያላስተናገደ ብቸኛው ክለብ ነው። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ20 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል።
ፋሲል ከነማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Dec 29, 2025 87
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ፋሲል ከነማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ፋሲል ከነማ ባደረጋቸው በሊጉ 11 ጨዋታዎች አምስት ጊዜ ሲያሸንፍ ስድስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ዘጠኝ ግቦቹን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ21 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ እስከ አሁን ሽንፈት ያላስተናገደው ብቸኛ ክለብ ፋሲል ከነማ ነው። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በውድድር ዓመቱ 11 ጨዋታዎችን አድርጎ አምስቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ስምንት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ አራት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ20 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ፋሲል ከነማ ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ከሲዳማ ቡና በጊዜያዊነት ይረከባል። በሌላኛው መርሃ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ምሽት 12 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። መቀሌ 70 እንደርታ በሊጉ ካደረጋቸው 11 ጨዋታዎች መካከል ያሸነፈው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። አምስት ጊዜ ሲሸነፍ በተመሳሳይ አምስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 12 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ስድስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በሰባት ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በበኩሉ 11 ጨዋታዎችን አከናውኖ አምስቱን ሲያሸንፉ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በ11ዱ ጨዋታዎች ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ ሰባት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በ17 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው መቀሌ 70 እንደርታ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከባህር ዳር ከተማ ይጫወታሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በስምንት ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በ14 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ወላይታ ድቻ ከአርባ ምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ወላይታ ድቻ በ10 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። አርባምንጭ ከተማ በአምስት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛው ቡድን ነው። ሲዳማ ቡና ሊጉን በ22 ነጥብ እየመራ ነው። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት እስከ ታህሳስ 22 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
በአፍሪካ ዋንጫ ወደ ጥሎ ማለፍ የሚገቡ አገራት የሚለዩባቸው ወሳኝ ጨዋታዎች ይደረጋሉ
Dec 29, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ የመጨረሻ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ። በምድብ አንድ አዘጋጇ ሀገር ሞሮኮ ከዛምቢያ ምሽት አራት ሰዓት ላይ በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ጨዋታዋን ታደርጋለች። ሞሮኮ በምድቡ እስከ አሁን ሁለት ጨዋታዎች አድርጋ በአራት ነጥብ ምድቡን እየመራች ነው። ተጋጣሚዊ ዛምቢያ በሁለት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። አዘጋጇ ሀገር ማሸነፍ ወይም አቻ መውጣት ወደ ጥሎ ማለፍ በቀጥታ ያስገባታል። ተሸንፋም ምርጥ ሶስተኛ ሆና የማለፍ እድል አላት። ተጋጣሚዋ ዛምቢያ ወደ 16 ውስጥ የመግባት እድሏን ለማስፋት ማሸነፍ ይጠበቅበታል። በዚሁ ምድብ በተመሳሳይ ምሽት አራት ሰዓት ላይ ኮሞሮስ ከማሊ በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኮሞሮስ በአንድ ነጥብ አራተኛ፣ ማሊ በሁለት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። ኮሞሮስ ወደ ጥሎ ማለፍ ለመግባት ያላት ብቸኛ እድል ማሸነፍ ብቻ ነው። በአንጻሩ ማሊ ወደ 16 ውስጥ የመግባት እድሏ ሰፊ ነው። በተያያዘም የምድብ ሁለት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ። አንጎላ ከግብጽ ምሽት አንድ ሰዓት ላይ በአጋዲር ስታዲየም ይጫወታሉ። ከሁለት ጨዋታዎች አንድ ነጥብ ያገኘችው አንጎላ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ ይዛለች። አስቀድማ ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቷን ያረጋገጠችው ግብጽ በስድስት ነጥብ ምድቡን እየመራች ነው። አንጎላ ወደ ጥሎ ማለፉ ለመግባት የሚያስችላትን እድል ለማግኘት ግብጽ ማሸነፍ ይኖርባታል። ጨዋታው ለግብጽ ምድቡን በበላይነት ከማጠናቀቅ የዘለለ ትርጉም የለውም። በዚሁ ምድብ በተመሳሳይ ምሽት አንድ ሰዓት ላይ ዚምባቡዌ ከደቡብ አፍሪካ በማራካሽ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ዚምባቡዌ በአንድ ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። ወደ ጥሎ ማለፍ ለማግባት ያላት ብቸኛ አማራጭ ማሸነፍ ብቻ ነው። በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ደቡብ አፍሪካ ማሸነፍ ቀጥታ ወደ ጥሎ ማለፍ ያስገባታል። አቻ መውጣትን ወደ ቀጣዩ ዙር ሊያሳልፋት ይችላል። በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ያለው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ ዘጠነኛ ቀኑን ይዟል።
አልጄሪያ ጥሎ ማለፍ የገባች ሶስተኛ ሀገር ሆናለች
Dec 29, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አምስት ጨዋታ አልጄሪያ ቡርኪናፋሶን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሪያድ ማህሬዝ በ23 ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ማህሬዝ በአፍሪካ ዋንጫው ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ ሶስት ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን ይዟል። በጨዋታው ላይ አልጄሪያ የተሻለ ብልጫ ወስዳለች። ፈረንሳዊው የቀድሞ ኮከብ ዚነዲን ዚዳን ለአልጄሪያ በግብ ጠባቂነት የሚጫወተውን ልጁን ሉካ ዚዳንን ለተከታታይ ጨዋታ በስታዲየም ተገኝቶ ተከታትሏል። ሉካ በአፍሪካ ዋንጫው በተሰለፈባቸው ሁለት ጨዋታዎች ግብ አልተቆጠረበትም። በምድብ አምስት ሁለተኛ ድሏን ያስመዘገበችው አልጄሪያ በስድስት ነጥብ ከግብጽ እና ናይጄሪያ በመቀጠል ጥሎ ማለፍ የገባች ሶስተኛ ሀገር ሆናለች። ቡርኪናፋሶ በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። በዚሁ ምድብ ዛሬ በተደረገ ጨዋታ ሱዳን ኢኳቶሪያል ጊኒን 1 ለ 0 አሸንፋለች። የምድብ አምስት የመጨረሻ መርሃ ግብር ረቡዕ ታህሳስ 22 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ኢኳቶሪያል ጊኒ ከአልጄሪያ እና ሱዳን ቡርኪናፋሶ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በተጠባቂው ጨዋታ ኮትዲቯር እና ካሜሮን ነጥብ ተጋሩ
Dec 29, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ስድስት ጨዋታ ኮትዲቯር እና ካሜሮን አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በማራካሽ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ የማንችስተር ዩናይትዱ አማድ ዲያሎ በ51ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ ያስቆጠራት ግብ ኮትዲቯርን መሪ አድርጓል። አማድ በውድድሩ ላይ ሁለተኛ ግቡን ማስቆጠር ችሏል። የኮትዲቯሩ ተከላካይ ጊስላን ኮናን በ56ኛው ደቂቃ በራሱ ላይ ባስቆጠረው ግብ ካሜሮን አቻ ሆናለች። በ48ኛው ደቂቃ የኮትዲቯሩ ፍራንክ ኬሲ ያስቆጠራት ግብ በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ከጨዋታ ውጪ በመሆኑ ተሽሯል። ጨዋታው እንደ ተጠባቂነቱ ጠንካራ ፉክክር ተደርጎበታል። የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ፕሬዝዳንት ፓትሪስ ሞትሴፔ(ዶ/ር) በስታዲየሙ ተገኝተው ጨዋታውን ተመልክተዋል። የሪያል ማድሪድ ተጫዋቾች የሆኑት ኪሊያን ምባፔ እና ኦሪየር ቹዌሜኒ (ሁለቱም በትውልድ ካሜሮናዊ በዜግነት ፈረንሳዊ)፣ የካሜሮን የቀድሞ ተጫዋች አሌክሳንደር ሶንግ እንዲሁም የባርሴሎናው ጁል ኩንዴ (በትውልድ ቤኒናዊ በዜግነት ፈረንሳዊ) ጨዋታውን በስታዲየም ተገኝተው ተከታትለዋል። የካሜሮን እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት እና የቀድሞ ተጫዋች ሳሙኤል ኤቶ በስታዲየሙ ታድሟል። ጨዋታውን ከ35 ሺህ በላይ ተመልካቾች ተከታትለውታል። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ኮትዲቯር እና የአምስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ካሜሮን በተመሳሳይ አራት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ኮትዲቯር እና ካሜሮን አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። ዛሬ በምድብ ስድስት በተደረገ ጨዋታ ሞዛምቢክ ጋቦንን 3 ለ 2 አሸንፋለች። የምድብ ስድስት የመጨረሻ መርሃ ግብር ረቡዕ ታህሳስ 22 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ጋቦን ከኮትዲቯር እና ሞዛምቢክ ከካሜሮን ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ በምድቡ ወደ ጥሎ ማለፍ የሚገቡ ሀገራትን የሚለዩ ናቸው።
የምስራቅ አፍሪካዋ ሱዳን ኢኳቶሪያል ጊኒን በማሸነፍ የመጀመሪያ ድሏን አስመዘገበች
Dec 28, 2025 77
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አምስት ጨዋታ ሱዳን ኢኳቶሪያል ጊኒን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በመሐመድ አምስተኛ በተካሄደው ጨዋታ የኢኳቶሪያል ጊኒው ተከላካይ ሳውል ኮኮ በ73ኛው ደቂቃ በራሱ መረብ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ኢኳቶሪያል ጊኒ በኳስ ቁጥጥር ብልጫ ብትወስድም ሱዳን በፈጣን ሽግግር እና መልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴ የግብ እድሎችን ፈጥራለች። ውጤቱን ተከትሎ ከአፍሪካ ዋንጫ መስራች ሀገራት መካከል አንዷ የሆነችው ሱዳን በዘንድሮው ውድድር የመጀመሪያ ድሏን አስመዝግባለች። በምድብ አምስት በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እየተሳተፉ ከሚገኙ የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት መካከል ሱዳን የመጀመሪያን ድል ያገኘች ሀገር ሆናለች። ታንዛንያ እና ዩጋንዳ ሌሎች ተሳታፊ ሀገራት ናቸው። በምድቡ ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ኢኳቶሪያል ጊኒ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃን ይዛለች። በምድብ አምስት አልጄሪያ ከቡርኪናፋሶ ምሽት 2 ሰዓት ከ30 በፕሪንስ ሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ሞዛምቢክ በአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ድሏን አስመዘገበች
Dec 28, 2025 86
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ስድስት ጨዋታ ሞዛምቢክ ጋቦንን 3 ለ 2 አሸንፋለች። በአጋዲር ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ፋይሰል ባንጋል እና ዲያጎ ካሊላ በጨዋታ፣ ጌኒ ካታሞ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ፒዬር-ኤሜሪክ ኦቦሚያንግ እና አሌክስ ሞስኬቱ-ሙሶንዳ ለጋቦን ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጨዋታው በርካታ የግብ እድሎች የተፈጠሩበት ሲሆን ተመጣጣኝ እና አዝናኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ሞዛምቢክ በምድብ ስድስት የመጀመሪያ ድሏን በማስመዝገብ በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። በአንጻሩ ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ቦትስዋና ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ምድብ ምሽት አምስት ሰዓት ኮትዲቯር ከካሜሮን በማራካሽ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
የአፍሪካ እግር ኳስ ኃያላኑ ኮትዲቯር እና ካሜሮን የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Dec 28, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ)፦ የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሁለተኛ መርሃ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። በዕለቱ የምድብ አምስት እና ስድስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በምድብ ስድስት የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ ባለቤት ኮትዲቭዋር ከአምስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ካሜሮን ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በማራካሽ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ የእግር ኳስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ ኮትዲቭዋር ሞዛምቢክን፣ ካሜሮን ጋቦንን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ሁለቱ የአፍሪካ እግር ኳስ ኃያላን በአህጉራዊው መድረክ ሲገናኙ የአሁኑ ለስድስተኛ ጊዜ ነው። ሀገራቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የተገናኙት ሱዳን እ.አ.አ በ1970 ባዘጋጀችው ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በወቅቱ ካሜሮን 3 ለ 2 አሸንፋለች። እ.አ.አ በ1992 በሴኔጋል በተካሄደው 18ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በግማሽ ፍጻሜ ባደረጉት ጨዋታ ኮትዲቭዋር ካሜሮንን በመለያ ምት በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፋለች። ኮትዲቭዋር በፍጻሜው ጋናን በማሸነፍ ለመጀመሪያ ጊዜ አንስታለች። ቡድኖቹ ለመጨረሻ ጊዜ በአህጉራዊው መድረክ የተገናኙት ኢኳቶሪያል ጊኒ እ.አ.አ በ2015 ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በምድብ አራት በተደረገው ጨዋታ ኮትዲቭዋር በማክስ-አለን ግራዴል ጎል 1 ለ 0 አሸንፋለች። በአጠቃላይ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫው አምስት ጊዜ ተገናኝተው ካሜሮን ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ ኮትዲቭዋር ሁለት ጊዜ ድል ቀንቷታል። ኮትዲቭዋር የዘንድሮውን ጨምሮ ለ26ኛ ጊዜ እየተሳተፈች የምትገኝ ሲሆን ሁለት ጊዜ ዋንጫውን አንስታለች። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ናት። በአንጻሩ ለ22ኛ ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫው የተሳተፈችው ካሜሮን አምስት ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ ከግብጽ በመቀጠል ስኬታማዋ ሀገር ናት። በአፍሪካ እግር ኳስ ደማቅ ታሪክ ያላቸው ሁለቱ ሀገራት በጨዋታው ላይ ጠንካራ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። ጨዋታውን የሚያሸንፈው ቡድን ወደ ጥሎ ማለፍ ይገባል። በምድብ ስድስት ሌላኛው መርሃ ግብር ጋቦን ከሞዛምቢክ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 በአጋዲር ስታዲየም ይጫወታሉ። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያ ጨዋታ ካስተናገዱት ሽንፈት በኋላ የመጀመሪያ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። በተያያዘም የምድብ አምስት ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ አልጄሪያ ከቡርኪናፋሶ በሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም ይጫወታሉ። በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ አልጄሪያ ሱዳንን 3 ለ 0፣ ቡርኪናፋሶ ኢኳቶሪያል ጊኒን 2 ለ 1 አሸንፈዋል። በሌላኛው የምድቡ መርሃ ግብር ኢኳቶሪያል ጊኒ ከሱዳን ምሽት 12 ሰዓት ላይ በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ ስምንተኛ ቀኑን ይዟል።
ናይጄሪያ ጥሎ ማለፉን ተቀላቀለች
Dec 28, 2025 86
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት ጨዋታ ናይጄሪያ ቱኒዚያን 3 ለ 2 አሸንፋለች። ማምሻውን በፌዝ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቪክቶር ኦሲሜን፣ ዊልፍሬድ ንዲዲ እና አዴሞላ ሉክማን የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሞንታሳር ታልቢ በጨዋታ እና አሊ አብዲ በፍጹም ቅጣት ምት ለቱኒዚያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጨዋታው አዝናኝ እና ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ናይጄሪያ በስድስት ነጥብ ግብጽን ተከትሎ ጥሎ ማለፍ የገባች ሁለተኛዋ ሀገር ሆናለች። የመጀመሪያ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ቱኒዚያ በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ምድብ ዛሬ በተደረገ ጨዋታ ዩጋንዳ እና ታንዛንያ አንድ አቻ ተለያይተዋል። የምድብ ሶስት የመጨረሻ መርሃ ግብር ማክሰኞ ታህሳስ 21 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ዩጋንዳ ከናይጄሪያ እና ታንዛንያ ከቱኒዚያ ጋር ይጫወታሉ።
በምስራቅ አፍሪካ ደርቢ ዩጋንዳ እና ታንዛንያ አቻ ተለያዩ
Dec 27, 2025 121
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ሶስት መርሃ ግብር ዩጋንዳ እና ታንዛኒያ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በአል መዲና ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሳይመን ምሱቫ በ59ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠረው ጎል ታንዛንያን መሪ አድርጓል። ኡቼ ኢክፒዙ በ80ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፈው ግብ ዩጋንዳ አቻ ሆናለች። የዩጋንዳው አለን ኦኬሎ በ91ኛው ደቂቃ የሳተው የፍጹም ቅጣት ምት ሀገሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ እንዳታገኝ አድርጓታል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ዩጋንዳ እና ታንዛኒያ በምድቡ የመጀመሪያ ነጥባቸውን አግኝተዋል። በዚሁ ምድብ ናይጄሪያ ከቱኒዚያ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በፌዝ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
በተጠባቂው ጨዋታ አስቶንቪላ ቼልሲን በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Dec 27, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አስቶንቪላ ከመመራት ተነስቶ ቼልሲን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆአኦ ፔድሮ በ37ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ቼልሲ መሪ ሆኖ ቆይቷል። ከእረፍት መልስ ኦሊ ዋትኪንስ በ63ኛው እና በ84ኛው ደቂቃ ያስቆጠራቸው ግቦች አስቶንቪላን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አስጨብጧል። በሊጉ ስምንተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው አስቶንቪላ በ39 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቼልሲ በ29 ነጥብ ከነበረበት አራተኛ ደረጃ ወደ አምስተኛ ዝቅ ብሏል። በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ19ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አስቶንቪላ ከሊጉ መሪ አርሰናል ማክሰኞ ታህሳስ 21 ቀን 2018 ዓ.ም በኤምሬትስ ስታዲየም የሚያደርገው ጨዋታ በጉጉት ይጠበቃል።
በተጠባቂው ጨዋታ ሴኔጋል እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ነጥብ ተጋሩ
Dec 27, 2025 101
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አራት መርሃ ግብር ሴኔጋል እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በታንጀር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሴድሪክ ባካምቡ በ61ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን መሪ አድርጓል። ሳዲዮ ማኔ በ69ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፋት ግብ ሴኔጋል አቻ ሆናለች። የሁለቱ ብሄራዊ ቡድኖች ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ሴኔጋል እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በምድብ አራት በተመሳሳይ አራት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። በዚሁ ምድብ ዛሬ በተደረገ ጨዋታ ቤኒን ቦትስዋናን 1 ለ 0 አሸንፋለች። በምድቡ የመጨረሻ መርሃ ግብር ማክሰኞ ታህሳስ 21 ቀን 2018 ዓ.ም ቤኒን ከሴኔጋል እና ቦትስዋና ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ ወደ ጥሎ ማለፍ የሚገቡ ሀገራት የሚለዩባቸው ናቸው።
አርሰናል የሊጉን መሪነት ዳግም ተረከበ
Dec 27, 2025 117
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ18ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርሰናል ብራይተንን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማርቲን ኦዴጋርድ እና የብራይተኑ ጆርጂኒዮ ሩተር በራሱ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዲያጎ ጎሜዝ ለብራይተን ብቸኛውን ጎል ከመረብ አሳርፏል። በሊጉ 13ኛ ድሉን ያስመዘገበው አርሰናል በ42 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከማንችስተር ሲቲ ዳግም ተረክቧል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ብራይተን በ24 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በሌሎች ጨዋታዎች ሊቨርፑል በራያን ግራቨንበርች እና ፍሎሪያን ዊትዝ ግቦች ዎልቭስን 2 ለ 1 ሲያሸንፍ ሳንቲያጎ ቡዌኖ ለዎልቭስ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ብሬንትፎርድ ፉልሃምን 4 ለ 1፣ ፉልሃም ዌስትሃምን 1 ለ 0 ሲያሸንፍ በርንሌይ ከኤቨርተን ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ቼልሲ ከአስቶንቪላ በቪላ ፓርክ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ቤኒን በአፍሪካ ዋንጫው የመጀመሪያ ድሏን አስመዘገበች
Dec 27, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ አራት ጨዋታ ቤኒን ቦትስዋናን 1 ለ 0 አሸንፋለች። በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዮሃን ሮቼ በ28ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ላይ ቤኒን ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ማንችስተር ሲቲ ኖቲንግሃም ፎረስትን በማሸነፍ የሊጉ መሪ ሆነ በውድድሩ የመጀመሪያ ድሏን ያስመዘገበችው ቤኒን በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። በአንጻሩ ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ቦትስዋና ያለ ምንም ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። በዚሁ ምድብ ሴኔጋል ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በታንጀር ስታዲየም ይጫወታሉ።
ማንችስተር ሲቲ ኖቲንግሃም ፎረስትን በማሸነፍ የሊጉ መሪ ሆነ
Dec 27, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ኖቲንግሃም ፎረስትን 2 ለ 1 አሸንፏል። በሲቲ ግራውንድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቲጃኒ ራይንደርስ እና ራያን ቼርኪ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኦማሪ ሁትቺንሰን ለኖቲንግሃም ፎረስት ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ 13ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ በ40 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከአርሰናል በጊዜያዊነት ተረክቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኖቲንግሃም ፎረስት በ18 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። አርሰናል ምሽት 12 ሰዓት ላይ ከብራይተን የሚያደርገው ጨዋታ ይጠበቃል። መድፈኞቹ ካሸነፉ የሊጉን መሪነት መልሰው ይረከባሉ።