ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
አስቶንቪላ እና ኒውካስትል ዩናይትድ ነጥብ ተጋሩ
Aug 16, 2025 37
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 10/2017 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት ጨዋታ አስቶንቪላ እና ኒውካስትል ዩናይትድ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታው ኒውካስትል ዩናይትድ የነበረውን የኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድል ወደ ጎል መቀየር ተስኖታል። አስቶንቪላ በጨዋታው ደካማ እንቅስቃሴ አሳይቷል። የአስቶንቪላው ተከላካይ ኢዝሪ ኮንሳ በ66ኛው ደቂቃ በአንቶኒ ጎርደን ላይ በሰራው ጥፋት በቀጥታ ቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ቡድኑ ለ30 ደቂቃ በ10 ተጫዋች ለመጫወት ተገዷል። ኮንሳ በአዲሱ የውድድር ዓመት የቀይ ካርድ የተመለከተ የመጀመሪያው ተጫዋች ሆኗል። ብራይተን ከፉልሃም፣ አዲስ አዳጊው ሰንደርላንድ ከዌስትሃም ዩናይትድ እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከበርንሌይ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ አምስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ
Aug 16, 2025 60
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2017 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል። የዕለቱ የመክፈቻ መርሃ ግብር በአስቶንቪላ እና ኒውካስትል ዩናይትድ መካከል ከቀኑ 8 ሰዓት ከ30 በቪላ ፓርክ ስታዲየም ይካሄዳል። ወደ ሊቨርፑል የማምራት ከፍተኛ ፍላጎት ያሳደረው የኒውካስትል ዩናይትዱ አጥቂ አሌክሳንደር ኢሳቅ በዛሬው ጨዋታ አይሰለፍም። ተጫዋቹ በተያዘው ሳምንት ከዚህ በኋላ ለክለቡ መጫወት እንደማይፈልግ አሳውቋል። ብራይተን ከፉልሃም፣ አዲስ አዳጊው ሰንደርላንድ ከዌስትሃም ዩናይትድ አና ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከበርንሌይ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት የሚደረጉ ጨዋታዎች ናቸው። ዎልቨርሃምፕተን ዎንድረስ ከማንችስተር ሲቲ ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ በሞሊኒው ስታዲየም ይጫወታሉ። በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ትናንት በተደረገው የመክፈቻ ጨዋታ የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል ቦርንማውዝን 4 ለ 2 አሸንፏል። በሊጉ የመጀመሪያ ሳምንት ጨዋታዎች በመኪና አደጋ ህይወታቸውን ላጡት ዲያጎ ጆታ እና ወንድሙ አንድሬ ሲልቫን በማሰብ ተጫዋቾች በክንዳቸው ላይ ጥቁር መለያ ጨርቅ በማሰር ይጫወታሉ።
በቻን ውድድር በምድብ ሁለት ታንዛንያን ተከትሎ ማን ወደ ሩብ ፍጻሜ ያልፋል?
Aug 16, 2025 55
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮና (ቻን) የምድብ ሁለት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ከታንዛንያ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት በቤንጃሚን ምካፓ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሶስቱ የምድብ ጨዋታዎቿ ሽንፈት ያስተናገደችው ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን ደረጃ ይዛ ከውድድሩ መሰናበቷ ይታወቃል። የዛሬው ጨዋታ መርሃ ግብር ከማሟላት የዘለለ ትርጉም የለውም። በተቃራኒው ሶስት ጨዋታዎችን በማሸነፍ በዘጠኝ ነጥብ ምድቡን የምትመራው ታንዛንያ አስቀድሞ ለሩብ ፍጻሜ መግባቷ የሚታወስ ነው። ሀገራቱ ከዚህ ቀደም ሶስት ጊዜ ተገናኝተው ታንዛንያ ሁለት ጊዜ ስታሸንፍ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ አንድ ጊዜ ድል ቀንቷታል። በሌላኛው የምድብ ሁለት መርሃ ግብር ቡርኪናፋሶ ከማዳጋስካር በተመሳሳይ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት በአማኒ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቡርኪናፋሶ በሶስት ነጥብ አራተኛ ደረጃን የያዘች ሲሆን ከውድድሩ መሰናበቷ ይታወቃል። በአራት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ማዳጋስካር ጨዋታውን ካሸነፈች ተመሳሳይ ነጥብ ይዛ ሁለተኛ ደረጃን የያዘቸውን ሞሪታኒያን በግብ ክፍያ በልጣ ለሩብ ፍጻሜ ታልፋለች። በአንጻሩ ማዳጋስካር ነጥብ ከጣለች ሞሪታኒያ ታንዛንያን ተከትላ ሩብ ፍጻሜውን ትቀላቀላለች። ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም ብቸኛ ግንኙነታቸው እ.አ.አ በ2020 በዓለም አቀፍ የወዳጅነት ጨዋታ ያደረጉት ሲሆን ቡርኪናፋሶ 2 ለ 1 አሸንፋለች።
ኒጀር እና ደቡብ አፍሪካ አቻ ተለያዩ
Aug 16, 2025 46
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮና (ቻን) ምድብ ሶስት ኒጀር እና ደቡብ አፍሪካ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ትናንት ማምሻውን በማንዴላ ብሄራዊ ስታዲየም በተካሄደው መርሃ ግብር ደቡብ አፍሪካ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድል በመፍጠር ብልጫ ብትወስድም ጎል ማስቆጠር አልቻለችም። ውጤቱን ተከትሎ ደቡብ አፍሪካ በአምስት ነጥብ ሶስተኛ፣ ኒጀር በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን አምስተኛ ደረጃን ይዘዋል። በተያያዘም በዚሁ ምድብ በተደረገ ጨዋታ ጊኒ እና አልጄሪያ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል የውድድር ዓመቱን በድል ጀምሯል
Aug 16, 2025 48
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2017(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ጨዋታ ሊቨርፑል ቦርንማውዝን 4 ለ 2 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አዲስ ፈራሚው ሁጎ ኢኪቲኬ በ37ኛው ደቂቃ የአዲሱን የውድድር ዓመት የመጀመሪያ ጎል አስቆጥሯል። ከእረፍት መልስ ኮዲ ጋፕኮ በ49ኛው ደቂቃ ሁለተኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። አንቶዋን ሴሜንዮ በ64ኛው እና በ76ኛው ደቂቃ ያስቆጠራቸው ግቦች ቦርንማውዝን አቻ አድርጓል። ተቀይሮ የገባው ፌዴሪኮ ኪዬዛ በ89ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠራት ጎል ሊቨርፑልን ዳግም መሪ አድርጓል።በቀያዮቹ ማሊያ የመጀመሪያ የሊግ ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። የአምናው የሊጉ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ መሐመድ ሳላህ በ95ኛው ደቂቃ የማሳረጊያዋን ግብ አስቆጥሯል። በጨዋታው ቀያዮቹ የተሻለ ብልጫ ወስደው ተጫውተዋል። ይሁንና በተከላካይ ክፍል መስመራቸው ላይ ክፍተት ታይቷል። ቦርንማውዝ በፈጣን የመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴ ተጋጣሚውን ፈትኖ አምሽቷል። የቦርንማውዙ ዴቪድ ብሩክስ የሊጉን የመጀመሪያ ቢጫ ካርድ ተመልክቷል። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ የውድድር ዓመቱን በድል አሐዱ ብሎ ጀምሯል። በጨዋታው በመኪና አደጋ ህይወቱ ያለፈው ዲያጎ ጆታ ታስቦ አምሽቷል። የእንግሊዝ ሊግ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል።
ጊኒ እና አልጄሪያ ነጥብ ተጋርተዋል
Aug 15, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 9/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮና (ቻን) የምድብ ሶስት ጨዋታ ጊኒ እና አልጄሪያ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ካምፓላ በሚገኘው ማንዴላ ብሄራዊ ስታዲየም በተደረገው መርሃ ግብር ኢስማኤል ካማራ በ62ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ጎል ጊኒ መሪ መሆን ችላለች። ጨዋታው በጊኒ አሸናፊነት ተጠናቀቀ ሲባል ሶፊያን ባያዚድ በ88ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ግብ ለአልጄሪያ ወሳኝ አንድ ነጥብ አስገኝታለች። አልጄሪያ በጨዋታው ያገኘቻቸውን በርካታ የግብ እድሎች መጠቀም አልቻለችም። ውጤቱን ተከትሎ አልጄሪያ በአምስት ነጥብ ሁለተኛ፣ ጊኒ በአራት ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። በዚሁ ምድብ ኒጀር ከደቡብ አፍሪካ ምሽት 2 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በአፍሪካ አገራት ሻምፒዮና የምድብ ሶስት ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ
Aug 15, 2025 93
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 9/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮና (ቻን) የ13ተኛ ቀን ውሎ የምድብ ሶስት ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ጊኒ ከአልጄሪያ ከቀኑ 11 ሰዓት ካምፓላ በሚገኘው ማንዴላ ብሄራዊ ስታዲየም ይጫወታሉ። በምድቡ ካደረገቻቸው ሶስት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ያገኘችው ጊኒ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ተጋጣሚዋ አልጄሪያ ከሁለት ጨዋታዎች አራት ነጥብ በመሰብሰብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። ማሸነፍ ለሁለቱ ሀገራት ለሩብ ፍጻሜ ለመግባት ያላቸውን እድል ያሰፋል። ቡድኖቹ ከዚህ ቀደም 15 ጊዜ ተገናኝተው በተመሳሳይ ስድስት ስድስት ጊዜ ሲያሸንፉ ሶስት ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። በ15ቱ ጨዋታዎች ሀገራቱ በተመሳሳይ 23 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በዚሁ ምድብ ምሽት ሁለት ላይ ኒጀር ከደቡብ አፍሪካ በማንዴላ ብሄራዊ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኒጀር በሁለት ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዳ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አምስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ተጋጣሚዋ ደቡብ አፍሪካ ከሁለት ጨዋታዎች አራት ነጥብ በማግኘት ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ኒጀር በውድድሩ ለመቆየት ያላትን ጭላንጭል ተስፋ ለማስቀጠል ከዛሬው ጨዋታ ሶስት ነጥብ ማግኘት ግዴታዋ ነው። በአንጻሩ ደቡብ አፍሪካ ካሸነፈች ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሏን ታሰፋለች። ሀገራቱ ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ሁለት የእርስ በእርስ ጨዋታዎች በተመሳሳይ አንድ አንድ ጊዜ አሸንፈዋል። የቻን ውድድር በኬንያ፣ ታንዛንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል
በአዲስ አበባ ሁሉንም የስፖርት ዓይነቶች ያማከሉ እና ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቁ የስፖርት ማዘውተሪያዎች እየተገነቡ ነው
Aug 15, 2025 101
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 9/2017(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ ሁሉንም የስፖርት ዓይነቶች ያማከሉና ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቁ የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎች በስፋት እየተገነቡ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ገለጸ፡፡ የቢሮው ኃላፊ በላይ ደጀን ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ስፖርት መልካም ስብዕና ያለው፣ በአካል፣ በአዕምሮና በስነ ልቦና ብቁና ንቁ የሆነ ሀገር ተረካቢ ትውልድ ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። ስፖርት ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነት፣ መተሳሰብና አብሮነትን በማጎልበት ማህበራዊ መስተጋብርን ለማጠናከር ከፍተኛ ሚና እንዳለውም ተናግረዋል። ስፖርት ለስራ ዕድል ፈጠራና ለኢንቨስትመንት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው በመሆኑ ቢሮው መሰረተ ልማትን ለማስፋት ዘርፈ ብዙ ተግባራት በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከአራት ዓመት በፊት በከተማዋ የነበሩ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ከአራት መቶ እንደማይበልጡ አስታውሰው፥ ለመሰረተ ልማት ግንባታ በተሰጠው ትኩረት አሁን ላይ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎቹ 1ሺህ 530 መድረሳቸውን አንስተዋል። ሁሉንም የስፖርት ዓይነቶች ያማከሉና ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቁ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ግንባታ ተጠናክሮ መቀጠሉንም ተናግረዋል። ከዚህ በፊት ለእግር ኳስ እና አትሌቲክስ ስፖርት ብቻ አገልግሎት ሲሰጡ የነበሩ ስፍራዎች በአሁኑ ጊዜ የቅርጫት፣ የእጅና የመረብ ኳስ፣ የጠረጴዛና ግራውንድ ቴኒስ የስፖርት ዓይነቶችን እንዲያካትቱ እየተሰራ መሆኑን አክለዋል፡፡ የተገነቡት የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ለታዳጊዎችና ወጣቶች ስፖርታዊ ብቃት መዳበር ምቹ ሁኔታን ከመፍጠር ባለፈ፥ ከተማዋ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን እንድታስተናግድ የሚያግዙ ናቸው ብለዋል። የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎቹ ነዋሪዎች በሚኖሩበት አካባቢ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ጤንነታቸውን እንዲጠብቁ እድል መፍጠራቸውንም ጠቁመዋል፡፡ ይህም አብሮነትን ባህል ያደረገ ማህበረሰብ ለመገንባት የሚያግዝ ከመሆኑም ባለፈ ብቁና ንቁ ዜጋን በመፍጠር የሀገራችን የብልፅግና ጉዞ እውን የሚያደርግ ነው ብለዋል። ከስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ግንባታ ጎን ለጎን ቢሮው ታዳጊ ስፖርተኞች ማፍራት ላይ ትኩረት ማድረጉንም ቢሮ ሀላፊው ጨምረው ገልጸዋል። በከተማው ተገንብተው አገልግሎት በመስጠት ላይ ከሚገኙ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች መካከል የጉለሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 08 ጉለሌ 03 ሜዳ ስፖርት ማዘውተሪያ አንዱ ነው፡፡ ታዳጊ ፅዮን ዋሲሁን እና እስጢፋኖስ ፀጋዬ ምቹ የስፖርት ማዘውተሪያ በአቅራቢያቸው መገንባቱ የስፖርት ክህሎታቸውን ለማሳደግ እድል እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል፡፡ በአራዳ ክፍለ ከተማ ወረዳ 05 አፍንጮ በር ስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራ ያገኘናቸው ታዳጊ ሱዴት ነሱር እና ብሩክ መንግስቱ በበኩላቸው ምቹና ዘመናዊ የስፖርት ማዘውተሪያ መኖሩ የእግር ኳስ ህልማቸውን ለማሳካት አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል።
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ከሁለት ቢሊዮን ፓውንድ በላይ የወጣባቸውን ታላላቅ ከዋክብት ይዞ ዛሬ ይጀመራል
Aug 15, 2025 110
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 9/2017(ኢዜአ)፦ በዘንድሮው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የዝውውር መስኮት የወጣው ወጪ ከዚህ ቀደም የነበሩ ክብረ ወሰኖችን የሰባበረ ነው። ክለቦች እስከ አሁን በአጠቃላይ ከሁለት ቢሊዮን ፓውንድ በላይ ገንዘብ አውጥተዋል። ፍሎሪያን ዊትዝ፣ ብራያን ምቡዌሞ፣ ቪክቶር ዮኬሬሽ፣ ማቲያንስ ኩንሃ፣ ሁጎ ኢኬቲኬ እና ቤንጃሚን ሴስኮ ብዙ ገንዘብ ከወጣባቸው ተጫዋቾች መካከል ይጠቀሳሉ። ሊቨርፑል እና ቼልሲ በርካታ ገንዘብ በማፍሰስ በቀዳሚነት ስፍራ ላይ ተቀምጠዋል። ዘንድሮ የሊጉ ክለቦች ያወጡት ረብጣ ገንዘብ አዲሱን የውድድር ዓመት የበለጠ አጓጊ እና ጠንካራ ፉክክር የሚታይበት ያደርገዋል ተብሎ ይጠበቃል። የ2025/26 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል እና ቦርንማውዝ በሚያደርጉት ጨዋታ ጅማሮውን ያገኛል። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ላይ በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ይካሄዳል። ሊቨርፑል ባለፈው ሳምንት በኮሙዩኒቲ ሺልድ ፍጻሜ በክሪታል ፓላስ በመለያ ምት ተሸንፎ ዋንጫ ማጣቱ ይታወቃል። ቀያዮቹ እንደ ሁጎ ኢኪቲኬ፣ ፍሎሪያን ዊትዝ እና ጀርሚ ፍሪምፖንግ ያሉ ተጫዋቾችን ቢያስፈርምም በቅድመ ውድድር ጨዋታዎች ላይ ያለው የተከላካይ መስመር ክፍተት ዋንኛ ስጋቱ ሆኗል። ቡድኑ የማጥቃት አቅሙን እንዳጠናከረው ሁሉ የተከላካይ ክፍሉን ጠንካራ ማድረግ እንዳለበት እየተገለጸ ይገኛል። ቦርንማውዝ ዲን ሀውሰን፣ ኢሊያ ዛባርኒይ እና ሚሎስ ኬርኬዥን መሸጡ የተከላካይ ክፍሉን አሳስቶታል። በአንቶዋን ሴሜንዮ፣ ኢቫኒለሰን እና ኤመርሰን የሚመራው የፊት መስመር በፈጣን መልሶ ማጥቃት የሚየያደርገው እንቅስቃሴ ለተጋጣሚው ፈታኝ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል። ሁለቱ ቡድኖች ከዚህ ቀደም 24 ጊዜ ተገናኝተው ሊቨርፑል 19 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ሲይዝ ቦርንማውዝ 2 ጊዜ ድል ቀንቶታል። 3 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። የ46 ዓመቱ አንቶኒ ቴይለር ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጀመሪያ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ነሐሴ 12 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል።
ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝታለች
Aug 15, 2025 73
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 9/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ ሀገራት ሻምፒዮና (ቻን) የምድብ አንድ መርሃ ግብር ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አንጎላን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ትናንት ማምሻውን በማንዴላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጄፕቴ ኪታምባላ ቦላ እና ጆናታን ሞኮንዚ ካቱምቡዌ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በስድስት ነጥብ ተመሳሳይ ነጥብ ባላት ሞሮኮ በግብ ክፍያ ተበልጣ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። የሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሏን የተሻለ አድርጋለች። ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው አንጎላ በአራት ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዛ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በዚሁ ምድብ ትናንት በተደረገ ጨዋታ ሞሮኮ ዛምቢያን 3 ለ 1 አሸንፋለች። ኬንያ ምድቡን በሰባት ነጥብ እየመራች ነው። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከሞሮኮ፣ ዛምቢያ ከኬንያ የሚያደርጓቸው የመጨረሻ የምድብ ጨዋታዎች ወደ ሩብ ፍጻሜ የሚያልፉ ሁለት ሀገራትን ይለያሉ።
የጃፓን ካራቴ ሾቶ ኢትዮጵያ ሻምፒዮና በቀጣዩ ሳምንት በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Aug 14, 2025 174
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 8/2017(ኢዜአ)፦ 4ኛው የጃፓን ካራቴ ሾቶ ኢትዮጵያ ሻምፒዮና ከነሐሴ 16 እስከ 18 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ይደረጋል። ውድድሩን አስመልክቶ የጃፓን ካራቴ ሾቶ ፌዴሬሽን ኢትዮጵያ ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። በሻምፒዮናው ላይ በሁሉቱም ጾታዎች ከኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች የተውጣጡ 300 ስፖርተኞች እንደሚሳተፉበት ተገልጿል። አካል ጉዳተኞችም በውድድሩ ላይ ይሳተፋሉ። በታዳጊዎች፣ በወጣቶች እና አዋቂዎች የእድሜ ክልል የተለያዩ የውድድር አይነቶች ይደረጋሉ። የኢትዮጵያ ካራቴ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ሙሉነህ ጎሳዬ የጃፓን ካራቴ ሾቶ ኢትዮጵያ ፌዴሬሽን የሚያካሂደው ሻምፒዮና ለሌሎች ውድድሮች ልምድ የሚቀሰምበት መሆኑን ተናግረዋል። ፌዴሬሽኑ ሻምፒዮናው በስኬት እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አመልክተዋል። የጃፓን ካራቴ ሾቶ ፌዴሬሽን ኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት ሰለሞን ዘውዱ ሻምፒዮናውን የተሻለ እና ስኬታማ ለማድረግ የሚያስፈልገው ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል። ፌዴሬሽኑ ስፖርቱን ለማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝም ተናግረዋል። በሻምፒዮናው ሜዳሊያ የሚያገኙ ስፖርተኞች የገንዘብ ሽልማት እንደሚበረከትላቸው ከኢትዮጵያ ካራቴ ፌዴሬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል። በ20ኛው ክፍለ ዘመን እንደተጀመረ የሚነገርለት የጃፓን ካራቴ ሾቶ ባህላዊ እና ዘመናዊ ስልትን አጣምሮ የያዘ የካራቴ ስፖርት አይነት ነው። ስፖርተኞች ለረጅም ጊዜ ጽንተው የሚቆዩባቸው የአቋቋም አይነቶች (Stances) ፣ የሽንጥ ተለዋዋጭ እንቅስቃሴ እና በፍጥነት ስልቶችን መቀያየር (ካታ) የስፖርቱ ዋንኛ መገለጫ ባህሪያት ናቸው። ካራቴ ሾቶ ለስብዕና ግንባታ እና ጤና አጠባበቅ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው የዘርፉ ባለሙያዎች ይገልጸሉ። ስፖርቱ በዓለም ደረጃ በዓለም አቀፉ ካራቴ ፌዴሬሽን፣ በሀገር ውስጥ በኢትዮጵያ ካራቴ ፌዴሬሽን እውቅና ያገኘ ነው።
በቻን ውድድር ሞሮኮ ዛምቢያን አሸነፈች
Aug 14, 2025 78
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 8/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ ሀገራት ሻምፒዮና (ቻን) የምድብ አንድ ጨዋታ ሞሮኮ ዛምቢያን 3 ለ 1 ረታለች። በማንዴላ ብሄራዊ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ መሐመድ ራቤ ህሪማ፣ ኡሳማ ላምሉዊ እና ሳቢር ቡጅሪን የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አንድሪው ፒሪ ለዛምቢያ የማስተዛዘኛዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ድሉን ተከትሎ ሞሮኮ በስድስት ነጥብ ከነበረችበት አራተኛ ደረጃ ወደ ሁለተኛ ከፍ ብላለች። ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሏንም አስፍታለች። በውድድሩ ሶስተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ዛምቢያ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አምስተኛ ደረጃን በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በዚሁ ምድብ ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከአንጎላ ይጫወታሉ።
በቻን ውድድር የምድብ አንድ ጨዋታዎች ተጠባቂ ናቸው
Aug 14, 2025 91
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 8/2017(ኢዜአ)፦ 12ኛ ቀኑን ባስቆጠረው የስምንተኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮና (ቻን) የምድብ አንድ ሶስተኛ ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ። ሞሮኮ ከዛምቢያ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ በካሳራኒ ስታዲየም ይጫወታሉ። በሁለት የምድብ ጨዋታዎቿ ሶስት ነጥብ ያገኘችው ሞሮኮ በሶስት ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። በአንጻሩ ዛምቢያ እስከ አሁን ባደረገቻቸው ሁለት ጨዋታዎች ተሸንፋ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አምስተኛ ደረጃን ይዛለች። ሞሮኮ ካሸነፈች ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሏን የበለጠ ታሰፋለች። ተጋጣሚዋ ዛምቢያ በውድድሩ ላይ ለመቆየት ከዛሬው ጨዋታ ሶስት ነጥብ መውሰድ አለባት። ሁለቱ ሀገራት ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 20 ጨዋታዎች ሞሮኮ 12 ጊዜ ስታሸንፍ ዛምቢያ 6 ጊዜ ድል ቀንቷታል። 2 ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በዚሁ ምድብ ምሽት 2 ሰዓት ላይ አንጎላ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አንጎላ በአራት ነጥብ ሁለተኛ፣ የሁለት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ማሸነፍ ለሁለቱም ቡድኖች ወደ ሩብ ፍጻሜው የማለፍ እድላቸውን ከፍ ያደርገዋል። ሀገራቱ 13 ጨዋታዎችን እርስ በእርስ አድርገው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ 7 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዛለች። አንጎላ 2 ጊዜ ስታሸንፍ 4 ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥተዋል። ቻን በኬንያ፣ ታንዛንያ እና ዩጋንዳ ጣምራ አዘጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። ውድድሩ በአገር ውስጥ ሊግ የሚገኙ ተጫዋቾች ብቻ የሚሳተፉበት ነው።
ሞሪታኒያ ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሏን ያሰፋችበትን ወሳኝ ድል ተቀዳጅታለች
Aug 14, 2025 91
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 8/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ ሀገራት ሻምፒዮና (ቻን) የምድብ ሁለት ጨዋታ ሞሪታኒያ ቡርኪናፋሶን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ትናንት ማምሻውን በቤንጃሚን ምካፓ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አላሳን ዲዮፕ በመጀመሪያው አጋማሽ ጭማሪ ደቂቃዎች ላይ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያዋን ጎል አስቆጥሯል። የቡርኪናፋሶ የአማካይ ተጫዋች አብዱላዬ ቱሬ በ41ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ይህም ቡርኪናፋሶን ከእረፍት መልስ በ10 ተጫዋች እንድትጫወት አስገድዷታል። ውጤቱን ተከትሎ በምድቡ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው ሞሪታኒያ ነጥቧን ወደ ሰባት ከፍ በማድረግ ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሏን ሰፊ አድርጋለች። በአንጻሩ ሁለተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ቡርኪናፋሶ በሶስት ነጥብ አራተኛ ደረጃን የያዘች ሲሆን አንድ ጨዋታ እየቀራት ከውድድሩ ተሰናብታለች። በዚሁ ምድብ በተካሄደ ሌላኛው ጨዋታ ማዳጋስካር ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ምድቡን በዘጠኝ ነጥብ የምትመራው ታንዛንያ ወደ ሩብ ፍጻሜ ማለፏ ይታወቃል።
ፒኤስጂ ቶተንሃም ሆትስፐርስን በማሸነፍ የአውሮፓ አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫን አነሳ
Aug 14, 2025 116
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 7/2017(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ፒኤስጂ ቶተንሃም ሆትስፐርስን በመለያ ምት በመርታት አሸናፊ ሆኗል። ማምሻውን በጣልያን በሚገኘው ብሉኢነርጂ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሚኪ ቫን ደ ቬን በ39ኛው እና ክርስቲያን ሮሜሮ በ48ኛው ደቂቃ ባሳረፉት ጎል ቶተንሃም ሆትስፐር መሪ ሆኖ ነበር። ቶተንሃም አሸነፈ ሲባል ተቀይረው የገቡት ካንግ ኢን ሊ በ85ኛው ደቂቃ እና ጎንካሎ ራሞስ በ93ኛው ደቂቃ ባስቆጠሩት ግብ ፒኤስጂ አቻ ሆኗል። ቡድኖቹ በመደበኛው 90 ደቂቃ ሁለት አቻ በመለያየታቸው ጨዋታው ቀጥታ ወደ መለያ አምርቷል። በዚህም ፒኤስጂ 4 ለ 3 በማሸነፍ የአውሮፓ አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫን ለመጀመሪያ ጊዜ አንስቷል። ፒኤስጂ ፍሰት ያለው ኳስ ለመጫወት የተቸገረ ሲሆን በተከላካይ፣ የአማካይ እና አጥቂ ክፍሎቹ ላይ የቅንጅት ችግር ታይቷል። ቡድኑ በመጨረሻዎቹ የጨዋታ ደቂቃዎች ያሳየው ማንሰራራት ወደ ጨዋታው እንዲመለስ አድርጎታል። ሉዊስ ኤነሪኬ ጣልያናዊውን ግብ ጠባቂ ጂያንሉዊጂ ዶናሩማን ከዛሬ ጨዋታ ስብስብ ውጪ ማድረጋቸው ትችት እንዲያስተናግዱ አድርጓቸዋል። ፒኤስጂ በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ዋንጫውን በማንሳት ድንቅ የውድድር ዓመቱን በደማቅ ሁኔታ አሳርጓል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በጨዋታው በተደራጀ መከላከል፣ በመልሶ ማጥቃት እንቅስቃሴ እና በቆሙ ኳሶች በመጠቀም የተሻለ ብቃት አሳይቷል። የሰሜን ለንደኑ ቡድን ከዩሮፓ ሊግ ቀጥሎ ሁለተኛ ዋንጫውን የማንሳት ህልሙ አልተሳከም። የአውሮፓ አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ እና የዩሮፓ ሊግ አሸናፊ የሚያደርጉት ጨዋታ ነው።
ማዳጋስካር ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝታለች
Aug 13, 2025 133
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 7/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ ሀገራት ሻምፒዮና (ቻን) የምድብ ሁለት መርሃ ግብር ማዳጋስካር ማዕከላዊ ሪፐብሊክን 2 ለ 0 አሸንፋለች። በቤንጃሚን ምካፓ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቶኪ ኒያና ራኮቶንድራቤ እና ላላና ራፋኖሜዛንትሶአ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በጨዋታው ማዳጋስካር በተጋጣሚዋ ላይ ብልጫ ወስዳለች። ውጤቱን ተከትሎ ማዳጋስካር በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ወደ ሩብ ፍጻሜ የመግባት እድሏን አለምልማለች። ሶስተኛ ሽንፈቷን ያስተናገደችው ማዕከላዊ ሪፐብሊክ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አምስተኛ ደረጃን በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በዚሁ ምድብ በአሁኑ ሰዓት ሞሪታንያ ከቡርኪናፋሶ ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛሉ። ምድቡን በዘጠኝ ነጥብ የምትመራው ታንዛንያ ወደ ሩብ ፍጻሜ ማለፏ ይታወቃል።
የቻን የምድብ የመጨረሻ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ
Aug 13, 2025 104
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 7/2017 (ኢዜአ)፡- በስምንተኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮና (ቻን) የ11ኛ ቀን ውሎ የምድብ ሁለት አራተኛ ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ማዳጋስካር ከማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ከቀኑ 11 ሰዓት በቤንጃሚን ምካፓ ብሄራዊ ስታዲየም ይጫወታሉ። በሁለት የምድብ ጨዋታዎቿ አንድ ነጥብ ያገኘችው ማዳጋስካር አራተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። ተጋጣሚዋ ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ሁለት ሽንፈት አስተናግዳ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አምስተኛ ደረጃን ይዛለች። ሁለቱ ቡድኖች ከዚህ ቀደም ሰባት ጊዜ እርስ በእርስ ተገናኝተው ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ሶስት ጊዜ ስታሸንፍ ማዳጋስካር ሁለት ጊዜ ድል ቀንቷታል። ሁለት ጊዜ አቻ ወጥተዋል። በጨዋታዎቹ ሁለቱም ሀገራት በተመሳሳይ 11 ግቦችን አስቆጥረዋል። ቡድኖቹ ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ ማሸነፍ ብቻ ሳይሆን በምድቡ ያሉ የሌሎች ቡድኖች ውጤት ይጠብቃሉ። በዚሁ ምድብ ምሽት 1 ሰዓት ሞሪታኒያ ከቡርኪናፋሶ በቤንጃሚን ምካፓ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በምድቡ ሞሪታኒያ በአራት ነጥብ ሁለተኛ፣ ቡርኪናፋሶ በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ሞሪታኒያ ካሸነፈች ወይም አቻ ከወጣች ቀጥታ ወደ ሩብ ፍጻሜው ትገባለች። ቡርኪናፋሶ ወደ ሩብ ፍጻሜው ለማለፍ የግዴታ ማሸነፍ አለባት። ሀገራቱ ከዚህ ቀደም 10 ጊዜ ተገናኝተው ቡርኪናፋሶ 6 ጊዜ ድል ሲቀናት ሞሪታኒያ 1 ጊዜ አሸንፋለች። 3 ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥተዋል። ምድብ ሁለትን በዘጠኝ ነጥብ የምትመራው ታንዛንያ ወደ ሩብ ፍጻሜ ማለፏ ይታወቃል።
ፒኤስጂ እና ቶተንሃም ሆትስፐርስ የአውሮፓ አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫን ለማንሳት ይጫወታሉ
Aug 13, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 7/2017(ኢዜአ)፦ የአውሮፓ አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በፈረንሳዩ ፒኤስጂ እና በእንግሊዙ ቶተንሃም ሆትስፐርስ መካከል ዛሬ ይደረጋል። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ላይ በጣልያኑ ዩዲኒዜ ክለብ ሜዳ ብሉኢነርጂ ስታዲየም ይካሄዳል። ፒኤስጂ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፣ ቶተንሃም ሆትስፐርስ የዩሮፓ ሊግ ሊግ አሸናፊ መሆናቸውን ተከትሎ ለፍጻሜው ጨዋታ ደርሰዋል። የፈረንሳዩ ቡድን በሻምፒዮንስ ሊጉ ፍጻሜ ኢንተር ሚላንን 5 ለ 0 በማሸነፍ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ማንሳቱ የሚታወስ ነው። በስፔናዊው ሉዊስ ኤነሪኬ የሚመራው ቡድን የፈረንሳይ ሊግ 1፣ የፈረንሳይ ጥሎ ማለፍ እና የፈረንሳይ አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫዎችንም አንስቷል። ፒኤስጂ በዘንድሮው የፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ ለፍጻሜ ደርሶ በቼልሲ ያልተጠበቀ የ3 ለ 0 ሽንፈት ማስተናገዱ የሚታወስ ነው። በአንጻሩ እ.አ.አ በ2024/25 በአንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 17ኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀው ቶተንሃም ሆትስፐርስ በዩሮፓ ሊግ ፍጻሜ ማንችስተር ዩናይትድ በማሸነፍ የቀጣዩ ዓመት የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎን አግኝቷል። የሰሜን ለንደኑ ቡድን በሊጉ መጥፎ የሚባል የውድድር ጊዜ አሳልፏል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከ41 ዓመት በኋላ ክለቡን ለአውሮፓ ክብር ያበቁትን አሰልጣኝ አንጌ ፖስትኮግሉን ማሰናበቱ ያልተጠበቀ ውሳኔ ነበር። በምትካቸው የብሬንትፎርድ አሰልጣኝ የነበሩትን ቶማስ ፍራንክን ሾሟል። ሁለቱ ክለቦች ከዚህ በፊት እርስ በእርስ የተገናኙት እ.አ.አ 2006 የቅድመ ውድድር የአቋም መለኪያ ሲሆን ቶተንሃም ሆትስፐርስ 3 ለ 0 አሸንፏል። ቡድኖቹ በውድድር ጨዋታዎች ላይ ከዚህ ቀደም ተገናኝተው አያውቁም። ፒኤስጂ ለአውሮፓ አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ሲጫወት የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን እ.አ.አ 1996 ከጁቬንቱስ ጋር ተጫውቶ ሽንፈት አጋጥሞታል። ቶተንሃም ሆትስፐር ለውድድሩ ፍጻሜ ሲቀርብ የአሁኑ የመጀመሪያ ጊዜ ነው። የፈረንሳዩ ክለብ ካለበት ድንቅ ብቃት አንጻር ጨዋታውን የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት አግኝቷል። ዝቅተኛ የማሸነፍ ግምት ያገኘው ቶተንሃም ሆትስፐርስ በእግር ኳስ ሁልጊዜ የሚባለውን ያልተጠበቀ ድል ሊያስመዘግብ ይችላል። የ37 ዓመቱ ፓርቹጋላዊ ጆአኦ ፒንሄሮ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
በስምንተኛው የአፍሪካ ሀገራት ሻምፒዮና(ቻን) ጨዋታ ሱዳን ናይጄሪያን አሸነፈች
Aug 12, 2025 101
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 6/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ ሀገራት ሻምፒዮና (ቻን) የምድብ አራት ጨዋታ ሱዳን ናይጄሪያን ባልተጠበቀ ሁኔታ 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት ረታለች። ማምሻውን በቤንጃሚን ምካፓ ብሄራዊ ስታዲየም በተደረገው መርሃ ግብር የአማካይ ተጫዋቹ አብደል ራኦፍ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ዋሊልዲን ከድር በፍጹም ቅጣት እና የናይጄሪያው ሊኦናርድ ንጌንጌ በራሱ ግብ ላይ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ሱዳን የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወሰድባትም ለግብ የቀረቡ እድሎችን በመፍጠር ተሽላ ተገኝታለች። ውጤቱን ተከትሎ ሱዳን ነጥቧን ወደ አራት ከፍ በማድረግ ተመሳሳይ ነጥብ ያላትን ሴኔጋልን በግብ ክፍያ በልጣ የምድቡ መሪ ሆናለች። ሁለተኛውን ሽንፈቷን ያስናገደችው ናይጄሪያ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ በመያዝ ከውድድሩ የተሰናበተች የመጀመሪያ ሀገር ሆናለች። በዚሁ ምድብ ዛሬ በተደረገ ጨዋታ የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ሴኔጋል ከኮንጎ ብራዛቪል አንድ አቻ ተለያይታለች። በመጨረሻው የምድብ መርሃ ግብር ሴኔጋል ከሱዳን፣ ናይጄሪያ ከኮንጎ ብራዛቪል ነሐሴ 13 ቀን 2017 ዓ.ም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ሴኔጋል እና ኮንጎ ብራዛቪል ነጥብ ተጋሩ
Aug 12, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 6/2017(ኢዜአ)፦ በስምንተኛው የአፍሪካ ሀገራት ሻምፒዮና(ቻን) በምድብ አራት መርሃ ግብር ሴኔጋል እና ኮንጎ ብራዛቪል አንድ አቻ ተለያይተዋል። በቤንጃሚን ምካፓ ብሄራዊ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዴቻን ሙሳቩ በ19ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ኮንጎ ብራዛቪልን መሪ አድርጋ ነበር። ይሁንና በ82ኛው ደቂቃ ጆሴፍ ላዩሴ ሳምብ ከመረብ ጋር ያገናኛት ጎል ለሴኔጋል ወሳኝ አንድ ነጥብ አስገኝታለች። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የቻን አሸናፊ ሴኔጋል በአራት ነጥብ በምድብ መሪነቷ ቀጥላለች። ኮንጎ ብራዛቪል በሁለት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ትከተላለች። በዚሁ ምድብ ሱዳን ከናይጄሪያ ምሽት 2 ሰዓት በቤንጃሚን ምካፓ ብሄራዊ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።