ስፖርት
ሪያል ማድሪድ ጁቬንቱስ በማሸነፍ ለሩብ ፍጻሜ አልፏል
Jul 2, 2025 18
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/2017 (ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ማለፍ ተጠባቂ መርሃ ግብር ሪያል ማድሪድ ጁቬንቱስን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻዉን በሃርድ ሮክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የ21 ዓመቱ አጥቂ ጎንዛሎ ጋርሺያ በ54ኛው ደቂቃ ከትሬንት አሌክሳንደር አርኖልድ የተሻገረለትን ኳስ በግሩም ሁኔታ በግንባሩ ገጭቶ በማስቆጠር ሎስ ብላንኮሶቹን አሸናፊ አድርጓል። ተስፈኛው ወጣት አጥቂ ጋርሺያ በውድድሩ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ ሶስት ከፍ አድርጓል። ሪያል ማድሪድ በጨዋታው የተሻለ ኳስ ቁጥጥር የነበረው ሲሆን ለግብ የቀረቡ እድሎችንም መፍጠር ችሏል። ጉዳት ላይ የነበረው ኪሊያን ምባፔ ተቀይሮ በመግባት በዓለም ዋንጫው የመጀመሪያ ተሳትፎውን አድርጓል። ጁቬንቱስ በመልሶ ማጥቃት ግብ ለማስቆጠር ወደ ሜዳ ይዞ የገባው የጨዋታ ስልት ውጤታማ አልነበረም። ውጤቱን ተከትሎ ሪያል ማድሪድ የሩብ ፍጻሜ ትኬቱን ቆርጧል። ከቦሩሲያ ዶርትሙንድ እና ሞንቴሬይ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። በጥሎ ማለፉ የመጨረሻ መርሃ ግብር ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ከሞንቴሬይ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ በሜርሴዲስ-ቤንዝ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የአውሮፓ ስመ ገናናዎቹ  ሪያል ማድሪድ እና ጁቬንቱስ ጨዋታ ተጠባቂ ነው 
Jul 1, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/2017 (ኢዜአ)፦ በፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር የመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 4 ሰዓት ላይ በሀርድ ሮክ ስታዲየም ሪያል ማድሪድ ከጁቬንቱስ የሚያደርጉት ጨዋታ የዓለም እግር ኳስ አፍቃሪያን ቀልባቸውን ጥለውበታል። የአምስት ጊዜ የፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ አሸናፊው ሪያል ማድሪድ በምድብ ስምንት በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ በመሆን ማጠናቀቁ ይታወቃል። በውድድሩ የመጀመሪያ ተሳትፎውን እያደረገ የሚገኘው ጁቬንቱስ በምድብ ሰባት ስድስት ነጥብ በማግኘት ሁለተኛ ደረጃን ይዞ ወደ ጥሎ ማለፉ ገብቷል። የአውሮፓ ኃያላኑ ሪያል ማድሪድ እና ጁቬንቱስ በሁሉም ውድድሮች እስከ አሁን 21 ጊዜ ተገናኝተዋል።   ሪያል ማድሪድ 10 ጊዜ በማግኘት ውስን ብልጫ ወስዷል። ጁቬንቱስ 9 ጊዜ ሲያሸንፍ 2 ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። በ21ዱ ጨዋታዎች ሪያል ማድሪድ 26 ግቦችን ሲያስቆጥር ጁቬንቱስ 25 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሁለቱ ክለቦች ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ2017 በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ፍጻሜ ነበር። በካርዲፍ በተካሄደው ጨዋታው ሪያል ማድሪድ 4 ለ 1 በማሸነፍ ዋንጫውን አንስቷል። በአውሮፓ እግር ኳስ ታሪክ ውስጥ ትልቁ የክለቦች ባላንጣነት ማሳያ ተደርጎ የሚጠቀሰው የቡድኖቹ ፍልሚያ ሁሌም ጠንካራ እና እልህ አስጨራሽ ፉክክር የሚደረግበት ነው። ሪያል ማድሪድ እና ጁቬንቱስ የየሊጋቸውን ዋንጫ በተመሳሳይ 36 ጊዜ በማንሳት የበላይነቱን ይዘዋል። በአውሮፓ መድረክ ሪያል ማድሪድ 15 ጊዜ የሻምፒዮንስ ሊጉን ዋንጫ ከፍ በማድረግ ስኬታማ መሆን የቻለ ክለብ ነው። ጁቬንቱስ ሁለት ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫን አንስቷል። የእግር ኳስ ባለሙያዎች ከወቅታዊ ብቃት አንጻር ሪያል ማድሪድ ጁቬንቱስን በጠባብ የግብ ልዩነት ሊያሸንፍ ይችላል የሚል ግምታቸውን አስቀምጠዋል። በጥሎ ማለፍ የመጨረሻ መርሃ ግብር ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ከሞንቴሬይ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ በሜርሴዲስ ቤንዝ ስታዲየም ይጫወታሉ።   ቦሩሲያ ዶርትሙንድ በሰባት ነጥብ የምድብ ስድስት መሪ፣ ሞንቴሬይ በምድብ አምስት በአምስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዘው ጥሎ ማለፍ ገብተዋል። ሁለቱ ክለቦች እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። የሁለቱ ጨዋታ አሸናፊዎች በሩብ ፍጻሜው ይገናኛሉ። በአሜሪካ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው የፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ ፒኤስጂ፣ ባየር ሙኒክ፣ ቼልሲ፣ ፓልሜራስ፣ አል ሂላል እና ፍሉሜኔንሴ እስከ አሁን ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀሉ ክለቦች ናቸው።
አል ሂላል ማንችስተር ሲቲን በማሸነፍ ባልተጠበቀ ሁኔታ ወደ ሩብ ፍጻሜ ገብቷል
Jul 1, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/2017 (ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ማለፍ መርሃ ግብር አል ሂላል ማንችስተር ሲቲን 4 ለ 3 አሸንፏል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በካምፒንግ ወርልድ ስታዲየም ተካሄዷል። ትናንት ከእኩለ ሌሊት በኋላ ጀምሮ እስከ ዛሬ ማለዳ በዘለቀው ጨዋታ በርናንዶ ሲልቫ በዘጠነኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ሲቲን መሪ አድርጓል። ማርኮስ ሊኦኖርዶ በ46ኛው እና ማልኮም በ56ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፏቸው ግቦች አል ሂላልን መሪ ሆኗል። ኤርሊንግ ሃላንድ በ55ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ ቡዱኑን አቻ አድርጓል። ቡድኖቹ በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሁለት አቻ በመለያየታቸው ወደ ተጨማሪ 30 ደቂቃ አምርተዋል። በተጨማሪ ሰዓት ካሊዶ ኩሊባሊ በ94ኛው ደቂቃ አል ሂላልን መልሶ መሪ ቢያደርግም ፊል ፎደን በ104ኛው ደቂቃ ማንችስተር ሲቲን በድጋሚ አቻ እንዲሆን አስችሏል። ማርኮስ ሊኦናርዶ በ112ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠራት ጎል አል ሂላልን ወደ ሩብ ፍጻሜ ልኳል። ልብ አንጠልጣይ ፋክክር በተደረገበት ጨዋታ የአል ሂላል የአልሸነፍ ባይነት ጽናት ባለድል አድርጓታል። ሁለት ግቦቹን ያስቆጠረው ማርኮስ ሊኦናርዶ የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። የአል ሂላል ግብ ጠባቂ ያሲን ቦኖ 10 ኳሶችን በማዳን ቡድኑን በጨዋታው እንዲቆይ በማድረግ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል። የሳዑዲ አረቢያው ቡድን የአውሮፓውን ክለብ በማሸነፍ ዓለም ያልጠበቀውን ውጤት አስመዝገቧል። አል ሂላል በሩብ ፍጻሜው ከፍሉሜኔንሴ ጋር የፊታችን አርብ ይጫወታል። ፍሉሜኔንሴ ትናንት ኢንተር ሚላንን 2 ለ 0 አሸንፏል።
ፍሉሜኔንሴ ኢንተር ሚላንን በማሸነፍ ለሩብ ፍጻሜ አለፈ
Jul 1, 2025 64
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 23/2017 (ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ማለፍ መርሃ ግብር ፍሉሜኔንሴ ኢንተር ሚላንን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በባንክ ኦፍ አሜሪካ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርጀንቲናዊው አጥቂ ጀርመን ካኖ ጨዋታው በተጀመረ በሶስተኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል የብራዚሉን ቡድን መሪ አድርጓል። ብራዚላዊው የአማካይ ተጫዋች ሄርኩሊስ በ94ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል የቡድኑን አሸናፊነት አረጋግጧል። በጨዋታው ኢንተር ሚላን በኳስ ቁጥጥር የተሻለ የነበረው ቢሆንም የፍሉሜኔንሴን አይበገሬ የተከላካይ ክፍል ሰብሮ መግባት አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ ፍሉሜኔንሴ ለሩብ ፍጻሜው ያለፈ አምስተኛ ቡድን ሆኗል። የደቡብ አሜሪካው ክለብ የአውሮፓውን ክለብ አሸንፏል። ፍሉሜኔንሴ በሩብ ፍጻሜው ከማንችስተር ሲቲ እና አል ሂላል አሸናፊ ጋር ይጫወታል። ማንችስተር ሲቲ ከአል ሂላል በካምፒንግ ወርልድ ስታዲየም ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
በፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ ሁለት የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ  
Jun 30, 2025 100
  አዲስ አበባ፤ ሰኔ 23/2017 (ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ የሶስተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ምሽት 4 ሰዓት ላይ ኢንተር ሚላን ከፍሉሜኔንሴ በባንክ ኦፍ አሜሪካ ስታዲየም ይጫወታሉ። የዘንድሮው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ፍጻሜ ተፈላሚ የነበረው ኢንተር ሚላን በምድብ አምስት በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ በመሆን ማጠናቀቀቁ የሚታወስ ነው። ፍሉሜኔንሴ በምድብ ስድስት በአምስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ወደ ጥሎ ማለፉ ገብቷል። ሁለቱ ክለቦች ከዚህ ቀደም እርስ በእርስ ተገናኝተው አያውቁም። ጨዋታው በኢንተር ሚላን የማጥቃት አቅም እና የፍሉሜኔንሴ አይበገሬ የተከላካይ ክፍል መካከል የሚደረግ ጦርነት የሚል ስያሜ አግኝቷል።   በዓለም ዋንጫው በሶስት ጨዋታዎች ሁለት ግቦችን ያስቆጠረው የ27 ዓመቱ የኢንተር ሚላን አጥቂ ላውታሮ ማርቲኔዝ እና የ40 የፍሉሜኔንሴ አንጋፋ ተከላካይ ቲያጎ ሲልቫ የሚኖራቸው ፍጥጫ ይጠበቃል። ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ በካምፒንግ ወርልድ ስታዲየም ማንችስተር ሲቲ ከአል ሂላል ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በምድብ ሰባት የነበረው ማንችስተር ሲቲ በዘጠኝ ነጥብ ወደ ጥሎ ማለፍ መግባቱ ይታወቃል። ሰማያዊዎቹ በውድድሩ የምድቡን ሁሉንም ጨዋታ ያሸነፈ ብቸኛ ክለብ ነው። በመጨረሻው የምድብ ጨዋታ ጁቬንቱስን 5 ለ 2 ሲያሸንፍ ያሳየው ድንቅ ብቃት የዋንጫ ተገማችነቱን የበለጠ አሳድጎታል።   የሳዑዲ አረቢያው አል ሂላል በምድብ ስምንት ሪያል ማድሪድን ተከትሎ በአምስት ሁለተኛ ደረጃን ይዞ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅሏል። ሁለቱ ክለቦች እ.አ.አ በ2012 በቅድመ ውድድር የወዳጅነት ጨዋታ ላይ ተገናኝተው አል-ሂላል 1 ለ 0 አሸንፏል። ማንችስተር ሲቲ ጨዋታውን የማሸነፍ ትልቅ ግምት ቢያገኝም ከተጋጣሚው ብርቱ ፉክክር ይጠብቀዋል። የጨዋታዎቹ አሸናፊዎች በሩብ ፍጻሜው የሚጫወቱ ይሆናል። በአሜሪካ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው የፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ ዛሬ 17ኛ ቀኑን ይዟል።
ፒኤስጂ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል
Jun 30, 2025 108
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 22/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር የአውሮፓ ሻምፒዮኑ ፒኤስጂ ኢንተር ሚያሚን 4 ለ ዐ በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በሜርሴዲስ-ቤንዝ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጇኦ ኔቬስ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ አሽራፍ ሃኪሚ እና የኢንተር ሚያሚው ቶማስ አቪሌስ በራሱ ግብ ላይ ቀሪዎቹን ጎሎች አስቆጥረዋል። ፒኤስጂ በጨዋታው በኢንተር ሚያሚ ላይ ፍጹም የጨዋታ የበላይነት የወሰደ ሲሆን የሚያሚ ተጫዋቾች ከራሳቸው የግብ ክልል ለመውጣትና ወደ ተጋጣሚ ቡድን መጫወቻ ስፍራ ለመድረስ እጅጉን ተቸግሮ ታይቷል። የፓሪሱ ክለብ ጠንካራ የመከላከል አቅም፣ አስደማሚ የመሐል ሜዳ ጨዋታ እና ማራኪ የማጥቃት እንቅስቃሴን ኢንተር ሚያሚ ሊቋቋም አልቻለም። በሊዮኔል ሜሲ እና ሉዊስ ሱዋሬዝ ልዩነት ፈጣሪነት ላይ ጥገኛ የሆነው ኢንተር ሚያሚ በጨዋታው የፒኤስጂ ፍጹም ቅጣት ክልል መድረስ ተራራን የመግፋት ያህል ከብዶት ነበር። የአውሮፓ ሻምፒዮኑ ፒኤስጂ ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀለ ሶስተኛ ቡድን ሆኗል።
ኢንተር ሚያሚ ፒኤስጂን በማሸነፍ ዓለምን ያስደምም ይሆን?
Jun 29, 2025 91
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 22/2017 (ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ ፒኤስጂ እና ኢንተር ሚያሚ ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። ጨዋታው ምሽት 1 ሰዓት ላይ በሜርሴዲስ ቤንዝ ስታዲየም ይደረጋል። የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊው ፒኤስጂ በነበረበት ምድብ ሁለት በስድስት ነጥብ የምድቡ መሪ በመሆን አጠናቋል። ኢንተር ሚያሚ በምድብ ሁለት በአምስት ሁለተኛ ደረጃን ይዞ ወደ 16 ውስጥ ገብቷል። ሁለቱ ክለቦች እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ የመጀመሪያው ነው። የኢንተር ሚያሚው አምበል እና አርጀንቲናዊው ኮከብ ሊዮኔል ሜሲ ከቀድሞ ክለቡ ፒኤስጂ ጋር የሚያደርገው ጨዋታ የዓለምን ትኩረት ስቧል። ሜሲ ከእ.አ.አ 2021 እስከ 2023 በፓሪሱ ክለብ የቆየ ሲሆን በቡድኑ በነበረው ቆይታ ደስተኛ እንዳልሆነ ገልጾ ነበር። ጨዋታው አርጀንቲናዊው ምትሃተኛ ፒኤስጂ ለሱ የሰጠው ግምት ትክክል አለመሆኑን የሚያሳይበት መልካም አጋጣሚ ፈጥሮለታል። የኢንተር ሚያሚው አሰልጣኝ ሃቪየር ማሻራኖ ሜሲ ከቀድሞ ክለቡ ጋር በንዴት መጫወቱ እኛን ይጠቅመናል፤ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሲሆን ምርጥ ብቃቱን የበለጠ አውጥቶ ያሳያል ሲል ገልጿል። ሜሲ፣ ማሻራኖ፣ ራሞን ጆርዲ አልባ እና ሉዊስ ሱዋሬዝ በባርሴሎና አሰልጣኛቸው ከነበሩት የአሁኑ የፒኤስጂ አለቃ ሉዊስ ኤነሪኬ ጋር ይገኛሉ። የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊው ፒኤስጂ ጨዋታውን የማሸነፍ ሰፊ ግምት አግኝቷል። ቡድኑ ባለው በጠንካራ ተከላካይ ክፍሉ እና በአስፈሪው የፊት መስመር ታግዞ ጨዋታውን እንደሚያሸንፍ የኳስ ልሂቃኑ በመናገር ላይ ይገኛሉ። ለጥቃት ተጋላጭ የተከላካይ ክፍል መስመር ያለው እና በውስን ተጫዋቾች ብቃት ላይ የተንጠለጠለው ኢንተር ሚያሚ ማንም ያልጠበቀውን ድል ሊያስመዘግብ ይችላል የሚሉ ተንታኞችም አልጠፉም። ሌላኛው የጥሎ ማለፍ ጨዋታ ፍላሚንጎ እና ባየር ሙኒክን ምሽት 5 ሰዓት ላይ በሃርድ ሮክ ስታዲየም ያገናኛል።     ፍላሚንጎ በምድብ አራት በሰባት ነጥብ አንደኛ፣ ባየር ሙኒክ በምድብ ሶስት በስስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዘው ማጠናቀቃቸው ይታወቃል። የታክቲክ ጦርነት ይደረግበታል በተባለበት በዚህ ጨዋታ ፍላሚንጎ ፈጣን የማጥቃት ሽግግሩ እና ኳስ ይዘው የሚጫወቱት አማካዮቹ በጨዋታው ላይ ልዩነት እንደሚፈጥሩ እየተነገረ ይገኛል። ባየር ሙኒክ ጥራት ያላቸውን ተጫዋቾች ሰብስቦ መያዙ እና የቡድን ጥልቀቱ በአንጻራዊነት የማሸነፍ እድል እንዲሰጠው አድርጎታል። የዛሬ ጨዋታ አሸናፊዎች በሩብ ፍጻሜው ይገናኛሉ።
ቼልሲ ሩብ ፍጻሜ ገብቷል
Jun 29, 2025 90
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 22/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ ሁለተኛ ጥሎ ማለፍ ጨዋታ ቼልሲ ቤኔፊካን 4 ለ 1 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በባንክ ኦፍ አሜሪካ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሪስ ጀምስ በ64ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ በቅጣት ምት ያስቆጠራት ግብ ቼልሲን መሪ አድርጓል። ጨዋታው በ86ኛው ደቂቃ ላይ በመጥፎ የአየር ንብረት ምክንያት ለሁለት ሰዓታት ተቀርጦ ነበር። ጨዋታው በድጋሚ ከተጀመረ በኋላ በ95ኛው ደቂቃ አንጌል ዲማሪያ በፍጹም ቅጣት ያስቆጠራት ጎል ቤኔፊካን አቻ አድርጓል። ቡድኖቹ በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አንድ አቻ በመለያየታቸው ወደ ጭማሪ 30 ደቂቃ አምርተዋል። በተጨማሪ ሰዓት ክርስቶፈር ንኩኩ በ108ኛው፣ ፔድሮ ኔቶ በ115ኛው እና ኬይርናን ዴውስበሪ-ሆል በ117ኛው ደቂቃ ያስቆጠሯቸው ግቦች ቼልሲ ተጋጣሚው አሸንፏል። ውጤቱን ተከትሎ ቼልሲ ሩብ ፍጻሜው የተቀላቀለ ሁለተኛ ቡድን ሆኗል። የምዕራብ ለንደኑ ክለብ በሩብ ፍጻሜው ከፓልሜራስ ጋር ይጫወታል። ፓልሜራስ ትናንት በጥሎ ማለፉ የመጀመሪያ ጨዋታ ቦታፎጎን 1 ለ 0 ማሸነፉ ይታወቃል። የቼልሲ እና ቤኔፊካ ጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር በዓለም ዋንጫው በመጥፎ የአየር ንብረት ምክንያት የተቋረጠ ሰባተኛ ጨዋታ ነው። ከፍተኛ ሙቀት እና መብረቅ ለጨዋታዎች መቋረጥ ዋንኛ ምክንያቶች ናቸው። ጨዋታዎች መቋረጣቸው የተጫዋቾችን ደህንነት ለመጠበቅ ያስችላል የሚል ሙገሳ ቢያገኝም ለረጅም ሰዓታት መቆሙ የጨዋታዎች ድባብ እና ፉክክር ላይ ጥላ አጥልቷል የሚል ትችትም እንዲያስተናግድ አድርጓታል።
ፓልሜራስ በፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀለ የመጀመሪያ ቡድን ሆኗል 
Jun 28, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ጥሎ ማለፍ ጨዋታ ፓልሜራስ ቦታፎጎን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሊንከን ፋይናንሻል ፊልድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሁሉቱ የብራዚል ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተው ወደ ተጨማሪ 30 ደቂቃ አምርተዋል። ተቀይሮ የገባው የ24 ዓመቱ ብራዚላዊ አጥቂ ፓውሊኒዮ በ100ኛው ደቂቃ ላይ በድንቅ አጨራረስ ያስቆጠራት ግብ ፓልሜራስን ባለድል አድርጋለች። የፓልሜራስ አምበል ጉስታቮ ጎሜዝ በ116ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። በጨዋታው በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድል በመፍጠር ፓልሜራስ የተሻለ ሆኖ ተገኝቷል። ቦታፎጎ በአመዛኙ መከላከል ያመዘነ የጨዋታ እንቅስቃሴ አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ ፓልሜራስ ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀለ የመጀመሪያው ቡድን ሆኗል። በሩብ ፍጻሜው ከቤኔፊካ እና ቼልሲ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። ቤኔፊካ ከቼልሲ ምሽት 5 ሰዓት ላይ በባንክ ኦፍ አሜሪካ ስታዲየም ይጫወታሉ።
በፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል 
Jun 28, 2025 104
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2017 (ኢዜአ)፦በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ ወደ ሩብ ፍጻሜ የሚገቡ ቡድኖች የሚለዩባቸው የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ። ምሽት 1 ሰዓት ላይ ፓልሜራስ ከቦታፎጎ በሊንከን ፋይናንሻል ፊልድ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ፓልሜራስ በምድብ አንድ በአምስት ነጥብ አንደኛ፣ ቦታፎጎ በምድብ ሁለት በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል። ሁለቱ የብራዚል ክለቦች በዘንድሮው ውድድር ጠንካራ ብቃታቸውን እያሳዩ ይገኛል። ቦታፎጎ በምድቡ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊውን ፒኤስጂን 1 ለ 0 ያሸነፈበት ውጤት ያልተጠበቀ ነበር። ቡድኖቹ ከዚህ ቀደም 106 ጊዜ ተገናኝተው ፓልሜራስ 40 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ቦታፎጎ በ32ቱ ድል ቀንቶታል። 34 ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥተዋል። በመጋቢት ወር በብራዚል ሴሪአ ባደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል። ሁለቱ የብራዚል ጠንካራ ቡድኖች ተመጣጣኝ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በሁለተኛው የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ከምሽቱ 5 ሰዓት ላይ ቤኔፊካ ከቼልሲ በባንክ ኦፍ አሜሪካ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቤኔፊካ በምድብ ሶስት በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ በመሆን አጠናቋል። ቼልሲ በምድብ አራት በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። ሁለቱ ቡድኖች እርስ በእርስ ሲገናኙ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ሶስት ጨዋታዎች ቼልሲ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። እ.አ.አ በ2013 በዩሮፓ ሊግ ፍጻሜ ተገናኝተው ቼልሲ 2 ለ 1 በማሸነፍ ዋንጫውን ማንሳቱ የሚታወስ ነው። በሩብ ፍጻሜው የፓልሜራስ እና ቦታፎጎ አሸናፊ ከቤኔፊካ እና ቼልሲ አሸናፊ ጋር ይጫወታሉ። የፊፋ ክለቦች ዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር እስከ ሰኔ 24 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚቆይ የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር (ፊፋ) አስታውቋል።
የስፖርት ዘርፉን ለማሳደግ የማዘውተሪያ ስፍራዎችን የማልማት ሥራ ይጠናከራል
Jun 27, 2025 143
ሀዋሳ፤ ሰኔ 20/2017 (ኢዜአ )በሲዳማ ክልል የስፖርት ዘርፉን ለማሳደግ የስፖርት የማዘውተሪያ ስፍራዎችን የማልማት ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለፁ። የክልሉ መንግስት ለሲዳማ ቡና እግር ኳስ ቡድን ያዘጋጀው የማበረታቻ ሽልማትና የዕውቅና መርሃ ግብር በሀዋሳ ከተማ ተካሄዷል።   የክልሉ ርዕሰ መስዳድር ለቡድኑ 19 ሚሊዮን ብር እና ሌሎች ሽልማቶችን ያበረከቱ ሲሆን የቡድኑ አባላትም ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ እጅ የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ተረክበዋል።   የ2017 የኢትዮጵያ ዋንጫ አሸናፊው የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ዋናው ቡድን ለ17 ተጫዋቾች ለእያንዳንዳቸው 200 ካሬ ሜትር የቤት መስሪያ ቦታና የገንዘብ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። በኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች የፕሪሚየር ሊግ አሸናፊ ለሆነው የሲዳማ ቡና እግር ኳስ ቡድን አባላትም የ4 ሚሊዮን ብር የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። በተመሳሳይም በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 3ኛ ደረጃን ይዞ ላጠናቀቀው የሲዳማ ቡና ሴቶች እግር ኳስ ቡድንም የ4 ሚሊዮን ብር ሽልማት ተበርክቷል።   በዘንድሮው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር 5ኛ ደረጃን ይዞ ላጠናቀቀው የሀዋሳ ከነማ እግር ኳስ ቡድን የ3 ሚሊዮን ብር እንዲሁም ለሲዳማ ቡና እግር ኳስ ቡድን ደጋፊዎች ማህበር የ1 ሚሊዮን ብር ሽልማት ተሰጥቷል። ሽልማቱን ተከትሎ መልዕክት ያስተላለፉት ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ ቡድኑ ባስመዘገበው ውጤት የክልሉ ህዝብና መንግስት ደስታ እንደተሰማው ገልፀዋል። የተገኘው ውጤት እንዲጠናከርም የክልሉ መንግስት በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ ጠቁመው ዘርፉን የመደገፍና በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች የስፖርት የማዘውተሪያ ስፍራዎችን የማልማት ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ እና የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎን ጨምሮ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።  
ሪያል ማድሪድ እና አል ሂላል ወደ ጥሎ ማለፉ ገብተዋል
Jun 27, 2025 109
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 20/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ የምድብ ስምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች ትናንት ከእኩለ ሌሊት በኋላ ተካሂደዋል። በሊንከን ፋይናንሻል ፊልድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሪያል ማድሪድ ሳልስበርግን 3 ለ 0 አሸንፏል። ቪኒሺየስ ጁኒየር፣ ፌዴሪኮ ቫልቬርዴ እና ጎንዛሎ ጋርሺያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ሪያል ማድሪድ በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ በመሆን ወደ ጥሎ ማለፉ ገብቷል። ሳልስበርግ በአራት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ከውድድሩ ተሰናብቷል። በዚሁ ምድብ በጂኦዲስ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አል ሂላል ፓቹካን 2 ለ 0 አሸንፏል። ሳሌም አል-ዶውሳሪ እና ማርኮስ ሊኦናርዶ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አል-ሂላል በአምስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅሏል። በምድቡ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ፓቹካ ያለ ምንም ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ ይዟል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የምድብ ጨዋታዎች ፍጻሜ አግኝተዋል። ሪያል ማድሪድ ከጁቬንቱስ፣ ማንችስተር ሲቲ ከአል ሂላል በጥሎ ማለፉ ይገናኛሉ። የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ከነገ ጀምሮ ይካሄዳሉ።
ማንችስተር ሲቲ ጁቬንቱስን በማሸነፍ የምድቡ መሪ በመሆን አጠናቋል
Jun 27, 2025 107
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 19/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች ዓለም ዋንጫ የምድብ ሰባት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ጁቬንቱስን 5 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በካምፒንግ ወርልድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዠርሚ ዶኩ፣ አርሊንግ ሃላንድ፣ ፊል ፎደን፣ ሳቪኒዮ እና የጁቬንቱሱ ተከላካይ ፒዬር ካሉሉ በራሱ ግብ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ቲን ኮፕማይነርስ እና ዱሳን ቭላሆቪች ለጁቬንቱስ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በጨዋታው ማንችስተር ሲቲ አስደናቂ ብቃት ያሳየ ሲሆን በተጋጣሚው ላይ ከፍተኛ ብልጫ ወስዷል። ሲቲ በዓለም ዋንጫው ሁሉንም የምድቡን ጨዋታዎች ያሸነፈ ብቸኛው ቡድን ሆኗል። ማንችስተር ሲቲ በዘጠኝ ነጥብ የምድቡ መሪ ሆኖ ተጠናቋል። ጁቬንቱስ በሰባት ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ሁለቱ ክለቦች ወደ ጥሎ ማለፍ መግባታቸው ይታወቃል። በዚሁ ምድብ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ አል አይ ዋይዳድ ካዛብላካን 2 ለ 1 አሸንፏል። ካኩ በጨዋታ እና ኮጆ ላባ በፍጹም ቅጣት ምት ለአል አይን ግቦቹን አስቆጥረዋል። ካሲአስ ማይሉላ ለዋይዳድ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ አል አይን በሶስት ነጥብ ሶስተኛና ዋይዳድ በአንድ ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዘው ውድድራቸውን አጠናቀዋል።
ሃይደር ሸረፋ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ኮከብ ተጫዋች ሆኖ ተመረጠ 
Jun 26, 2025 128
  አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2017 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መድን የአማካይ ተጫዋች ሃይደር ሸረፋ የ2017 ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ኮከብ ተጫዋች ሆኖ ተመርጧል።   የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ስሑል ሽሬ እና ኢትዮጵያ መድን ባደረጉት ጨዋታ ፍጻሜውን አግኝቷል። ከጨዋታው በኋላ የ2017 የኮከቦች ሽልማት ስነ ስርዓት ተካሄዷል። በዚሁ መሰረት የኢትዮጵያ መድን የአማካይ ተጫዋች ሃይደር ሸረፋ የዓመቱ ኮከብ ተጫዋች ሽልማትን አግኝቷል። የ210 ሺህ ብር ሽልማትም ተበርክቶለታል። የሃዋሳ ከተማው አጥቂ ዓሊ ሱሌይማን በ21 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ በመሆን የ200 ሺህ ብር ሽልማት አግኝቷል። ዓሊ ሱሌይማን በ2016 የውድድር ዓመትም በ20 ግቦች የሊጉ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ እንደነበር የሚታወስ ነው።   የኢትዮጵያ መድኑ አቡበከር ኑራ ኮከብ ግብ ጠባቂ እና የኢትዮጵያ መድኑ ገብረመድህን ኃይሌ ኮከብ አሰልጣኝ በመሆን በተመሳሳይ የ200 ሺህ ብር ሽልማት አግኝተዋል። ኮከብ ተስፈኛ ተጫዋች ሆኖ የተመረጠው የኢትዮጵያ ቡናው ይታገሱ ታሪኩ 105 ሺህ ብር ተሸልሟል። ኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ማኑኤ ወልደፃዲቅ የዓመቱ ምስጉን ዋና ዳኛ ሆነው የተመረጡ ሲሆን የ150 ሺህ ብር ተሸላሚ ሆነዋል። ኢንተርናሽናል ረዳት ዳኛ ሙስጠፋ መኪ የዓመቱ ምስጉን ረዳት ዳኛ በመሆን የ105 ሺህ ብር ተሸላሚ ሆነዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የእግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና ውድድር የሆሳዕና ከተማ አሸናፊ ሆነ
Jun 26, 2025 89
ሆሳዕና ፤ ሰኔ 19/2017(ኢዜአ)፡- የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሁለተኛው የእግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና ውድድር በሆሳዕና ከተማ አሸናፊነት ዛሬ ተጠናቀቀ። በሆሳዕና ከተማ ለተከታታይ 15 ቀናት ሲካሄድ በቆየው በዚሁ ውድድር የወራቤ ከተማ እና የእንደጋኝ ሻድጋር ክለቦች ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን አግኝተዋል።   በውድድሩ ማጠናቀቂያ ሥነ-ሥርዓት ላይ የክልሉ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌታቸው ሌሊሾ እንደገለጹት፤ ውድድሩ በክልሉ የአብሮነት እሴት እንዲጎለብት በማድረግ ረገድ አስተዋጽኦ አበርክቷል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ክልሉን በመወከል የሚጫወቱ ሶስት ክለቦችን ለመለየት ማስቻሉንም ጠቁመዋል።   የሆሳዕና ከተማ እግር ኳስ ክለብ አሰልጣኝ ክብረአብ እዮብ በሰጠው አስተያየት፤ የእግር ኳስ ሻምፒዮና ውድድሩ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት እንደሚያግዝ ገልጿል፡፡ በውድድሩ ክለቡ በአሸናፊነት ማጠናቀቁ በቀጣይ ለተሻለ ውጤት በትጋት እንዲሰራ እንደሚያበረታታው ተናግሯል። በውድድሩ አንደኛ ደረጃን በመያዝ ላጠናቀቀው ክለብ ዋንጫ እና የወቅር ሜዳሊያ እንዲሁም ሁለተኛ እና ሶሰተኛ ደረጃ ላገኙት ክለቦች ደግሞ የብር እና የነሐስ ሜዳሊያ ተበረክቶላቸዋል።   በመርሐ ግብሩ ማጠናቀቂያ ሥነ-ሥርዓት ላይ የክልል ፡ የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር አመራሮችና የስፖርት ቤተሰቦች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ተጠናቀቀ
Jun 26, 2025 89
  አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2017 (ኢዜአ)፦ በ2017 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጨረሻ ጨዋታ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ መድን ስሑል ሽሬን 3 ለ 0 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አቡበከር ሳኒ፣ ወገኔ ገዛኸኝ እና ዋንጫ ቱት የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ሻምፒዮኑ ኢትዮጵያ መድን በ73 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዞ የውድድር ዓመቱን አጠናቋል። በሊጉም 22ኛ ድሉን አግኝቷል። ኢትዮጵያ መድን በርካታ ግቦችን ያስቆጠረ፣ አነስተኛ የግብ መጠን ያስተናገደ እና በርካታ ነጥብ የሰበሰበ ቡድን ነው። ወደ ከፍተኛ ሊግ የወረደው ስሑል ሽሬ በ22 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። በውድድር ዓመቱም 18ኛ ሽንፈቱን አስተናግዷል። ጨዋታውን ተከትሎ መስከረም 10 ቀን 2017 ዓ.ም አሐዱ ብሎ የጀመረው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ከዘጠኝ ወራት ቆይታ በኋላ ዛሬ ፍጻሜውን አግኝቷል። ለመጀመሪያ ጊዜ የሊጉ አሸናፊ የሆነው ኢትዮጵያ መድን ዋንጫውን በመዝጊያ ስነ ስርዓቱ ይረከባል። በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ይሳተፋል።
የስፖርቱን ዘርፍ ህዝባዊ መሰረት እንዲኖረው በማድረግ ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ ይሰራል -ባህልና ስፖርት ሚኒስቴር
Jun 26, 2025 93
ጅማ፣ ሰኔ 19/2017 (ኢዜአ) የስፖርቱን ዘርፍ ህዝባዊ መሰረት እንዲኖረው በማድረግ ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ እንደሚሰራ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ገለፀ። በጅማ ከተማ ለአስር ቀናት በ26 የስፖርት ዓይነቶች ሲካሄድ የቆየው የስድስተኛው መላው ኢትዮጵያ የስፖርት ውድድር ዛሬ ተጠናቋል። በስፖርታዊ ውድድሩም በኦሮሚያ ክልል 224 ሜዳሊያ በማግኘት አንደኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ሲሆን አዲስ አበባ 220 እንዲሁም አማራ ክልል 143 ሜዳልያዎችን በማግኘት ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል።   በውድድሩ መዝጊያ ስነ-ስርዓት ላይም የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታው አቶ መኪዩ መሀመድ እንዳሉት ስፖርቱ ህዝባዊ መሰረት እንዲኖረው በልዩ ትኩረት እየተሰራ ነው። የስፖርቱን ዘርፍ በማነቃቃት እና ትኩረት እንዲያገኝ ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸው በዚህም ህዝቡ በባለቤትነት ተሳትፎ እንዲያደርግ ይሰራል ብለዋል። ስፖርት እያዝናና መቀራረብንና አብሮነትን የሚያጠናክር በመሆኑ በስፖርቱ የህዝቡን የእርስ በእርስ ትስስር ለማጎልበትም ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።   ዛሬ የተጠናቀቀው መላው ኢትዮጵያ ጨዋታዎች በዓለም መድረኮች ኢትዮጵያን የሚወክሉ ጠንካራ ስፖርተኞችን ለማፍራትም ትልቅ እድል የፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የኦሮሚያ ክልል የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ አቶ ሳዳት ነሻ በበኩላቸው፤ በክልሉ የስፖርት ዘርፉ ትልቅ ትኩረት እንደተሰጠው ገልጸዋል።   የክልሉ መንግስት የስፖርት ዘርፉን ለማሳደግ የሚያስችሉ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎችን ጨምሮ ዘርፉን ወደፊት ማምጣት የሚያስችሉ ስራዎች እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ''ስፖርት ወዳጅነትን እና ወንድማማችነትን የምናጎለብትበት ብሎም በዓለም የምንታወቅበት በመሆኑ ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት ይጠናከራል'' ብለዋል።  
በፊፋ ክለቦች የዓለም ዋንጫ የምድብ ጨዋታዎች ዛሬ ፍጻሜያቸውን ያገኛሉ 
Jun 26, 2025 98
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2017(ኢዜአ)፦ በፊፋ የክለቦች የዓለም ዋንጫ የምድብ ሰባት እና ስምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በምድብ ሰባት ጁቬንቱስ ከማንችስተር ሲቲ በፍሎሪዳ ካምፒንግ ወርልድ ስታዲየም ከምሽቱ 4 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ወደ ጥሎ ማለፉ መግባታቸውን ያረጋገጡት ጁቬንቱስ እና ማንችስተር ሲቲ በተመሳሳይ ስድስት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። ጨዋታው የምድቡ መሪ ሆኖ የሚያጠናቅቀውን ቡድን ይወስናል። በዚሁ ምድብ በተመሳሳይ ከምሽቱ 4 ሰዓት ላይ ዋይዳድ ካዛብላንካ ከአል አይን በኦዲ ፊልድ ስታዲየም ይጫወታሉ። በተመሳሳይ ሁለት ሽንፈትን በማስተናገድ ከውድድሩ የተሰናበቱት ዋይዳድ ካዛብላንካ እና አል አይን ያለ ምንም ነጥብ በግብ እዳ ተበላልጠው ሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። የቡድኖቹ ብቸኛ መጽናኛ በውድድሩ ድል አስመዝግቦ ወደ ሀገር ቤት መመለስ ነው። በምድብ ስምንት ሳልስበርግ ከሪያል ማድሪድ በሊንከን ፋይናንሻል ፊልድ ስታዲየም፣ አል ሂላል ከፓቹካ በጂኦዲስ ፓርክ ስታዲየም በተመሳሳይ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ሪያል ማድሪድ እና ሳልስበርግ በተመሳሳይ አራት ነጥብ በግብ ክፍያ ተባላልጠው አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። አሸናፊው ቡድን የምድቡ መሪ ሆኖ ወደ ጥሎ ማለፉ ይገባል። አቻ መውጣት በሂሳባዊ ስሌት ሁለቱንም ቡድኖች ወደ ቀጣዩ ዙር ሊያሸጋግራቸው ይችላል። አል ሂላል በሁለት ነጥብ ሶስተኛ እና ከውድድሩ የተሰናበተው ፓቹካ ያለ ምንም ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አል ሂላል ብቸኛ ወደ ጥሎ ማለፍ የሚያልፈው ተጋጣሚውን አሸንፎ ሳልስበርግ እና ሪያል ማድሪድ ከተሸናነፉ ነው። ፓልሜራስ፣ኢንተር ሚያሚ፣ ፒኤስጂ፣ ቦታፎጎ፣ ቤኔፊካ፣ ባየርሙኒክ፣ ፍላሚንጎ፣ ቼልሲ፣ ቦሩሲያ ዶርትሙንድ፣ ፍሉሚኔንሴ፣ ኢንተር ሚላን፣ ሞንቴሬይ ፣ ጁቬንቱስ እና ማንችስተር ሲቲ ጥሎ ማለፉን የተቀላቀሉ ቡድኖች ናቸው።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ይጠናቀቃል
Jun 26, 2025 97
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2017 (ኢዜአ)፦ የ2017 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ስሑል ሽሬ እና ሻምፒዮኑ ኢትዮጵያ መድን በሚያደርጉት የ36ኛ ሳምንት ጨዋታ ፍጻሜውን ያገኛል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። ወደ ከፍተኛ ሊግ የወረደው ስሑል ሽሬ በ22 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። በጊዜያዊ ዋና አሰልጣኝ መብራሃቶም ፍስሃ የሚመራው ስሑል ሽሬ በሊጉ ባደረጋቸው 33 ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሽንፈት ሲያስተናግድ 17 ጊዜ ደግሞ ሽንፈት አስተናግዷል። 13 ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ቡድኑ 22 ጎሎችን ሲያስቆጥር 43 ግቦችን አስተናግዷል። ስሑል ሽሬ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ (19) በመቀጠል በሊጉ በርካታ ሽንፈቶችን ያስተናገደ ቡድን ነው። ሻምፒዮኑ ኢትዮጵያ መድን በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 33 ጨዋታዎች 21 ጊዜ ሲያሸንፍ 5 ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። 7 ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። 46 ግቦችን ሲያስቆጥር 15 ግቦችን ተቆጥረውበታል። በገብረመድህን ኃይሌ የሚሰለጥነው ኢትዮጵያ መድን ከ33ቱ ጨዋታዎች 70 ነጥብ ሰብስቧል። በውድድር ዓመቱ በርካታ ግቦችን ያስቆጠረ፣ አነስተኛ የግብ መጠን ያስተናገደ እና በርካታ ነጥብ የሰበሰበ ቡድንም ነው። ኢትዮጵያ መድን ከጨዋታው በኋላ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የግሉ ያደረገውን የሊጉን ዋንጫ ይረከባል። በ2017 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመዝጊያ ስነ ስርዓት የኮከቦች ሽልማት ይካሄዳል። የዓመቱ ኮከብ ተጫዋች፣ የዓመቱ ኮከብ ተስፈኛ ተጫዋች፣ የዓመቱ ኮከብ ግብ ጠባቂ፣ የዓመቱ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ፣ የዓመቱ ኮከብ አሰልጣኝ፣ የዓመቱ ምስጉን ዋና ዳኛ እና የዓመቱ ምስጉን ረዳት ዳኛ ሽልማት ይበረከትላቸዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም