ቀጥታ፡
ስፖርት
አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ በ1 ሺህ 500 ሜትር ፍጻሜ ትወዳደራለች 
Sep 16, 2025 53
አዲስ አበባ፤ መስከረም 6 /2018 (ኢዜአ)፦ በ20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ ዛሬ በሚካሄደው የ1 ሺህ 500 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ ኢትዮጵያን ወክላ ትወዳደራለች። ውድድሩ ከቀኑ 10 ሰዓት ከ 05 ላይ ይካሄዳል። አትሌት ፍሬወይኒ ለዛሬው ፍጻሜ የደረሰችው የሁለት ዙር ማጣሪያዋን በብቃት በመወጣቷ ነው። ፍሬወይኒ እ.አ.አ በ2022 በአሜሪካ ኢውጅን በተካሄደው 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1 ሺህ 500 ሜትር ፍጻሜ ተወዳድራ አራተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቋ የሚታወስ ነው። አትሌቷ እ.አ.አ በ2023 በኢውጅ በተካሄደ ውድድር 3 ደቂቃ ከ55 ሴኮንድ ከ68 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓቷን አስመዝግባለች። ፍሬወይኒ እ.አ.አ በ2024 በግላስኮው በተደረገው 19ኛው የዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ1 ሺህ 500 ሜትር የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘቷ አይዘነጋም። በዛሬው የፍጻሜ ውድድር ላይ 14 አትሌቶች ይሳተፋሉ። ከፍጻሜው ውድድር በተጨማሪ ከቀኑ 7 ሰዓት ከ35 በሚካሄደው የ800 ሜትር ወንዶች የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ አትሌት ዮሐንስ ተፈራ ኢትዮጵያን ወክሎ ይሳተፋል። በምድብ ስድስት የሚወዳደረው አትሌት ዮሐንስ እ.አ.አ ጁላይ 5, 2025 በፈረንሳይ በተካሄደ ውድድር 1 ደቂቃ ከ44 ሴኮንድ ከ49 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱን የግል ምርጥ ሰዓት አስመዝግቧል። በሰባት ምድብ በሚካሄደው ማጣሪያ ከየምድቡ ከአንድ እስከ ሶስት የሚወጡ አትሌቶች ለግማሽ ፍጻሜው ያልፋሉ። አራተኛ ቀኑን በያዘው 20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ እስከ አሁን ሁለት የብር እና አንድ የነሐስ ሜዳሊያ አግኝታለች።
በትውልዱ የጋራ ርብርብ ለስኬት የበቃው የህዳሴ ግድብ በክልሉ ህዝብ ዘንድ ከፍተኛ መነሳሳት ፈጥሯል -አቶ አወሉ አብዲ
Sep 15, 2025 112
አዲስ አበባ፤ መስከረም 5 /2018(ኢዜአ)፦ በትውልዱ የጋራ ርብርብ ለስኬት የበቃው የህዳሴ ግድብ በኦሮሚያ ክልል ህዝብ ዘንድ ከፍተኛ መነሳሳት ፈጥሯል ሲሉ የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አወሉ አብዲ ገለጹ። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት መጠናቀቅን ምክንያት በማድረግ በኦሮሚያ ስፖርትና ወጣቶች ቢሮ አስተባባሪነት የክልሉ አመራሮችና ሰራተኞች የአካል ብቃት እንቅስቃሴ አድርገዋል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አወሉ አብዲ፤ የአሁኑ ትውልድ በጋራ ባደረገው ከፍተኛ ርብርብ የህዳሴን ግድብ በማሳካት አንጸባራቂ ውጤት ለአለም ማሳየት ችሏል። ይህም በክልሉ ህዝብ ዘንድም ሆነ በመላው ኢትዮጵያውያን ዘንድ ከፍተኛ መነሳሳት መፍጠሩን ገልጸው፤ በዚሁ መነሳሳትም ክልሉ ቀጣይነት ያለውን ሰላም በማጽናት የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ተግባራት ላይ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። ህዝቡ በህዳሴው ግድብ ፕሮጀክት ያሳየውን ትብብር በሌሎች የልማት ስራዎች ላይም አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አቶ አወሉ አንስተዋል።   አያይዘውም በክልሉ የተለያዩ የልማት ኢንሼቲቮችን ተግባራዊ በማድረግ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ተግባራት እንደሚከናወኑም አንስተዋል። እንዲሁም የመንግስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን በአንድ ማዕከል በማድረግ ህዝቡ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኝ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በስፖርታዊ እንቅስቃሴው ላይ ከተሳተፉት መካከል በክልሉ የህዳሴ ግድብ ህዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ዋና ስራ አስፈጻሚ ወይዘሮ ቆንጂት በቀለ እንዳሉት የክልሉ ህዝብ ከግድቡ ፕሮጀክት ጅማሮ አንስቶ በገንዘብና በዓይነት ድጋፍ ሲያደርግ ቆይቷል።   ለዘርፈ ብዙ ድጋፉ ህዝቡን ያመሰገኑት ወይዘሮ ቆንጂት በቀለ ድጋፉን በሌሎች የልማት ስራዎች ላይም አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል።
የኃይሌ ገብረስላሴ እና የፖል ቴልጋርት የአቴንስ ትንቅንቅ ሲታወስ
Sep 15, 2025 151
እ.አ.አ 1997 ስድስተኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በግሪክ አቴንስ የተካሄደበት ወቅት ነበር። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በሁለቱም ጾታዎች ተሳትፎ አድርጋለች። 5000 ሜትር፣ 3000 ሜትር መሰናክል፣ 10000 ሜትር እና ማራቶን በወንዶች እንዲሁም 1ሺህ 500፣ 5000 ሜትር፣ 10000 ሜትር እና ማራቶን ኢትዮጵያ በሴቶች የተሳተፈችባቸው ርቀቶች ነበሩ። የ10000 ሜትር ወንዶች ፍጻሜ በዓለም አትሌቲክስ ታሪክ ውስጥ ድንቅ የሚባል ፉክክር ከታየባቸው ውድድሮች መካከል በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀስ ነው። ውድድሩ የዓለም ኮከቡንና የኦሊምፒክ ሻምፒዮኑን ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ እና የኬንያውን የምንግዜም ተቀናቃኙን ፖል ቴርጋት ያገናኘ ነበር። ሁለቱ አትሌቶች በፍጻሜው ላይ የተገናኙት የብቃት ጫፍ ላይ በነበሩበት ወቅት ላይ ነው። የአቴንሱ ውድድር የአትሌቶቹ በወቅቱ እያደገ የመጣ ተቀናቃኝነት ላይ አዲስ የታሪክ ምዕራፍን የከፈተ እና ፉክክራቸው እ.አ.አ በ1990ዎቹ የረጅም ርቀት ውድድሮች በያኝ ነበር ማለት ይቻላል።   የ10000 ሜትር ፍጻሜው ሁሉም የአትሌቲክስ አፍቃሪ የገመተውን እልህ አስጨራሽ ፉክክር የተመለከተበት ነበር። ቴርጋት በውድድሩ የኃይሌን የ10000 ሜትር የበላይነት ለማስቆም የሮጠበት በአንጻሩ ኢትዮጵያዊው ኮከብ አትሌት ትዕግስት በተሞላበት፣ ከተቀናቃኙ ቅርብ ሆኖ ትንፋሹን በመለካትና ጉልበቱን በመጠበቅ ሮጧል። በመጨረሻዎቹ ዙሮች ውጥረቱ እያጋለ የመጣ ሲሆን ሁለቱ ታላላቅ አትሌቶች ከሌሎቹ አትሌቶች ተነጥለው በመውጣት ፉክክራቸውን ቀጠሉ። ቴርጋት ለማሸነፍ ቀድሞ ቢወጣም በድንቅ የአጨራረስ ብቃት የሚታወቀው ኃይሌ በመጨረሻው ዙር የአጸፋ ምላሹን ሰጠ። ኃይሌ የአንገት ለአንገት ትንቅንቁን በብቃት በመወጣት የአሸናፊነቱን መስመር ተሻግሮ የወርቅ ሜዳሊያ አጠለቀ። 27 ደቂቃ ከ24 ሴኮንድ ከ58 ማይክሮ ሴኮንድ አትሌቱ ያሸነፈበት ጊዜ ነው። ቴርጋት በ27 ደቂቃ ከ28 ሴኮንድ ከ56 ማይክሮ ሴኮንድ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቀቀ። የሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ወርቅ ኢትዮጵያ በአቴንሱ ሻምፒዮና ያገኘችው ብቸኛ ሜዳሊያ ነበር። የአቴንሱ ፍልሚያ የኃይሌን የበላይነት ዳግም ያሳየ ሲሆን ቴርጋት ቢሸነፍም እልህ አስጨራሽ ፉክክር አድርጓል። ሁለቱ ድንቅ አትሌቶች እ.አ.አ በ2020 በሲድኒ በተካሄደው 27ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በተመሳሳይ 10 ሺህ ሜትር ፍጻሜ በድጋሚ ተገናኝተው ዓለምን ቁጭ ብድግ ያሰኘ ፉክክር አድርገዋል። ኃይሌ አሁንም በሽርፍራፊ ሴኮንዶች ተቀናቃኙን አስከትሎ በመግባት አሸንፏል። የ1997ቱ የአቴንስ የዓለም ሻምፒዮና የ10000 ሜትር ወንዶች ፍጻሜ የሁለቱን የምንግዜም ድንቅ የረጅም ርቀት ሯጮች ብርቱ ፉክክር አንጥሮ ውድድር ሆኖ ሁሌም ሲወሳ ይኖራል።
ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በ3000 ሜትር መሰናክል ወንዶች ፍጻሜ ይሳተፋሉ
Sep 15, 2025 90
አዲስ አበባ፤ መስከረም 5/2018(ኢዜአ)፦ በ20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ የ3000 ሜትር መሰናክል ወንዶች የፍጻሜ ውድድር ይካሄዳል። ከቀኑ 9 ሰዓት ከ55 በሚካሄደው የፍጻሜ ውድድር ለሜቻ ግርማ፣ ጌትነት ዋለ እና ሳሙኤል ፍሬው ይሳተፋሉ። አትሌት ለሜቻ እ.አ.አ በ2023 በሀንጋሪ ቡዳፔስት በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና፣ እ.አ.አ በ2022 በአሜሪካ ኢውጂን በተደረገው 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እና በኳታር ዶሃ በተከናወው 17ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በርቀቱ በተመሳሳይ የብር ሜዳሊያዎችን አግኝቷል። ለሜቻ እ.አ.አ በ2023 በፓሪስ በተደረገው የዳይመንድ ሊግ ውድድር 7 ደቂቃ ከ52 ሴኮንድ ከ11 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት መሆኑ ይታወሳል። አትሌቱ በሻምፒዮናው ተሳትፎ ታሪክ የመጀመሪያውን ወርቅ ለማግኘት ከወቅቱ አሸናፊ ሞሮኳዊው ሶፊያን ኤል-ባካሊ ጋር የሚያደርገው ፉክክር ተጠባቂ ነው። በውድድሩ ላይ የሚሳተፉት ጌትነት ዋለ 8 ደቂቃ ከ5 ሴኮንድ ከ15 ማይክሮ ሴኮንድ እና ሳሙኤል ፍሬው 8 ደቂቃ ከ4 ሴኮንድ ከ34 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓታቸው ነው። በቶኪዮ እየተካሄደ ባለው 20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ እስከ አሁን ሁለት የብር እና አንድ የነሐስ ሜዳሊያ አግኝታለች።
ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉበት የ10000 ሜትር ወንዶች ፍጻሜ ዛሬ 9:30 ጀምሮ ይደረጋል
Sep 14, 2025 104
አዲስ አበባ፤ መስከረም 4/2018 (ኢዜአ)፦ በጃፓን ቶኪዮ እየተካሄደ የሚገኘው 20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል። ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 የ10000 ሜትር ወንዶች የፍጻሜ ውድድር ይካሄዳል። ሰለሞን ባረጋ፣ በሪሁ አረጋዊ እና ዮሚፍ ቀጄልቻ ኢትዮጵያን ወክለው ይወዳደራሉ። አትሌት ሰለሞን እ.አ.አ በ2023 በሀንጋሪ ቡዳፔስት በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ10000 ሜትር የነሐስ ሜዳሊያ ማግኘቱ የሚታወስ ነው። 26 ደቂቃ ከ34 ሴኮንድ ከ93 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቱ ነው። ሌላኛው ተወዳዳሪ አትሌት በሪሁ አረጋዊ በቡዳፔስት በተደረገው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ10000 ሜትር አራተኛ መውጣቱ አይዘነጋም። 26 ደቂቃ ከ31 ሴኮንድ ከ13 ማይክሮ ሴኮንድ የአትሌት በሪሁ የርቀቱ ይግል ምርጥ ሰዓቱ ሆኖ ተመዝግቧል። አትሌት ዮሚፍ ቀጄልቻ 26 ደቂቃ ከ31 ሴኮንድ ከ01 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የግል ምርጥ ሰዓቱ ነው። አትሌቱ በቡዳፔስቱ ሻምፒዮና በ5000 ሜትር ተሳትፎ አድርጎ ነበር። ከፍጻሜው ውድድር ውጪ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ5 በ1 ሺህ 500 ሴቶች ግማሽ ፍጻሜ ውድድር አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ ትወዳደራለች። አትሌት ፍሬወይኒ በምትወዳደርበት ምድብ አንድ ከአንድ እስከ ስድስት ያለውን ደረጃ ይዛ ካጠናቀቀች ለፍጻሜ ታልፋለች። በተጨማሪም ከሌሊቱ 9 ሰዓት ከ35 በሚካሄደው የ1 ሺህ 500 ሜትር ወንዶች የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ኤርሚያስ ግርማ እና መለሰ ንብረት ይሳተፋሉ። ኢትዮጵያ በ20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና መክፈቻ በትዕግስት አሰፋ በሴቶች ማራቶን የብር እና በ10000 ሜትር ሴቶች በጉዳፍ ጸጋይ አማካኝነት ማግኘቷ የነሐስ ሜዳሊያ አግኝታለች።
ኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና
Sep 13, 2025 91
በየሁለት ዓመቱ በዓለም አትሌቲክስ (በቀድሞ ስያሜው የዓለም አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር) አዘጋጅነት የሚካሄደው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከኦሊምፒክ ጨዋታና ከእግር ኳሱ የዓለም ዋንጫ ቀጥሎ፣ በግዝፈቱ የሚጠቀስ ስፖርታዊ ውድድር ነው። ነገር ግን ሻምፒዮናው ከተጀመረበት ከእ.አ.አ 1983 እስከ 1991 ሲካሄድ የነበረው በየአራት ዓመቱ ሲሆን በጃፓን ቶኪዮ እ.አ.አ በ1991 ከተካሄደው ሶስተኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በኋላ ውድድሩ በየሁለት ዓመቱ እንዲካሄድ መደረጉን የዓለም አትሌቲክስ መረጃ ያመለክታል። ሻምፒዮናው ለመጀመሪያ ጊዜ እ.አ.አ በ1983 በፊንላንድ ሄልሲንኪ ከተማ የተካሄደ ሲሆን በሻምፒዮናው ላይ ከ153 አገራት የተወጣጡ ከ1 ሺህ 300 በላይ አትሌቶች ተሳትፈውበታል። ለመጀመሪያ ጊዜ ሲከናወን ኢትዮጵያ በ10 አትሌቶች በ3000 ሜትር መሰናከል፣ 5000 ሜትር፣ 10000 ሜትር፣ ማራቶንና 20 ኪሎ ሜትር የእርምጃ ውድድሮች ተሳትፋለች። ከተሳተፉት አትሌቶች መካከል ከበደ ባልቻ በማራቶን ተወዳድሮ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ በሻምፒዮናው ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ለኢትዮጵያ ሜዳሊያ ማስገኘት የቻለ ሲሆን አፍሪካ በሻምፒዮናው ያገኘችው የመጀመሪያ ሜዳሊያ ሆኖ ተመዝግቧል። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው 15ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1987 በጣልያን ሮም ከተካሄደው ሁለተኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተሳትፋለች። ኢትዮጵያውያ የተሳተፉባቸው ውድድሮች በወንዶች 400 ሜትር፣ 800 ሜትር፣ 1500 ሜትር፣ 5000 ሜትር፣ 10000 ሜትር እና ማራቶን በሴቶች 400 ሜትር እንዲሁም መሰናክል ናቸው። በዚህ ውድድር ላይ ኢትዮጵያ ሜዳሊያ አላገኘችም። በመጀመሪያው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በወንድ አትሌቶች ብቻ በተመሰረተ ቡድን የተሳተፈችው ኢትዮጵያ በጣልያን ሮም በተከናወነው 2ኛው ውድድር ላይ የመጀመሪያዋን እንስት ተወካይ ይዛ መቅረቧን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል። በዚህ ዓለም አቀፍ ውድድር ላይ ሀገሯን በመወከል በ400 ሜትር መሰናክል የተወዳደረችው የመጀመሪያ እንስት አትሌትም የቀድሞዋ አትሌት የአሁኗ አሰልጣኝ ዘውዴ ኃይለማርያም ነች። 3ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በጃፓን ቶኪዮ ኦሊምፒክ ስታዲየም እ.አ.አ በ1991 የተካሄደ ሲሆን በውድድሩ ላይ ከ167 አገራት የተውጣጡ 1 ሺህ 517 አትሌቶች ተሳትፈዋል። በዚህ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በአትሌት ፊጣ ባይሳ አማካኝነት የብር ሜዳሊያ አግኝታለች፡፡ እ.አ.አ 1993 አራተኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በጀርመን ስቱትጋርት የተካሄደበት ዓመት ነው። በሻምፒዮናው በ10 ሺህ ሜትር የመጀመሪያው ወርቅና በ5 ሺህ ሜትር ውድድር ደግሞ የነሐስ ሜዳሊያ በሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ አማካኝነት ማግኘት ተችሏል። እንደዚሁም አትሌት ፊጣ ባይሳ ደግሞ ሌላ ነሐስ አክሎ ኢትዮጵያ ሶስት ሜዳሊያ አግኝታለች። እ.አ.አ በ1995 ጉተንበርግ ስዊድን በተካሄደው አምስተኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ በ10 ሺህ ሜትር ወርቅ በአትሌት ደራርቱ ቱሉ ደግሞ ብር የተገኘበት ሻምፒዮና ነበር፡፡ እ.አ.አ በ1997 ስድስተኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአቴንስ ግሪክ ሲካሄድ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ በ10 ሜትር ከፖል ቴርጋት ጋር ተናንቆ ወርቅ የተገኘበት ክስተት የሚዘነጋ አይደለም። ሰባተኛው ሻምፒዮና በስፔን ሲቪል ኢስታዲዮ ኦሊምፒኮ ዴ ላ ካርቱጃ ስታዲየም እ.አ.አ በ1999 ሲከናወን ልማደኛው ኃይሌ ገብረስላሴ በ10 ሺህ ሜትር ወርቅ፣ አሰፋ መዘገቡ ደግሞ ነሐስ ሜዳሊያ አስገኝተዋል። አትሌት ጌጤ ዋሜ በሴቶች 10 ሺህ ሜትር የወርቅ ሜዳሊያ በማግኘት በሻምፒዮናው ታሪክ የወርቅ ሜዳሊያ ያገኘች ሴት አትሌት መሆን ችላለች። አትሌት አየለች ወርቁ በ5 ሺህ እንዲሁም አትሌት ቁጥሬ ዱለቻ በ1 ሺህ 500 በተመሳሳይ የነሐስ ሜዳሊያዎችን አግኝተዋል። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በድምሩ 5 ሜዳሊያ በማግኘት ዘጠነኛ ደረጃን ይዛ ውድድሩን አጠናቃለች። እ.አ.አ በ2001 በካናዳ ኤድመንተን ስምንተኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተካሄደ ሲሆን በወንዶች ማራቶን አትሌት ገዛኸኝ አበራ በማሸነፍ በሻምፒዮናው ታሪክ በርቀቱ ለኢትዮጵያ የወርቅ ሜዳሊያ ማስገኘት ችሏል። አትሌት አሰፋ መዝገቡ በ10 ሺህ ሜትር ወንዶች የብር፣ በ5 ሺህ ሜትር ወንዶች ሚሊዮን ወልዴ የብር እና አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ የነሐስ ሜዳሊያ ለአገራቸው አስገኝተዋል። በሴቶች የ10 ሺህ ሜትር አትሌት ደራርቱ ቱሉ፣ ብርሃኔ አደሬ እና ጌጤ ዋሚ ከአንድ እስከ ሶስት በመውጣት አረንጓዴው ጎርፍ በኤድመንተን እንዲደምቅ አድርገዋል። አትሌት አየለች ወርቁ በ5 ሺህ ሜትር ሴቶች የነሐስ ሜዳሊያ ለአገሯ አምጥታለች። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በአጠቃላይ 8 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ከዓለም 7ኛ ደረጃ ይዛ በሻምፒዮናው ተሳትፎዋ የተሻለውን ደረጃ በመያዝ አጠናቃለች። እ.አ.አ. በ2003 በፈረንሳይ ፓሪስ በተካሄደው ዘጠነኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በወንዶች በ10 ሺህ ሜትር አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴና በስለሺ ስህን ከአንደ እስከ ሶስት ተከታትለው በመግባት የኢትዮጵያን የበላይነት ያረጋገጠ ድል አስመዝግበዋል። አትሌት ቀነኒሳ በ5 ሺህ ሜትር ወርቅ በማግኘት የድርብ ድል ባለቤት የሆነበት ታሪካዊ ውድድርም ነበር። በሴቶች 10 ሺህ ሜትር አትሌት ብርሃኔ አደሬና ወርቅነሽ ኪዳኔ ወርቅና ብር ማግኘት የቻሉ ሲሆን ጥሩነሽ ዲባባ ደግሞ በ5 ሺህ ሜትር ወርቅ አግኝታለች። 10ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተካሄደው የመጀመሪያ ሻምፒዮና በተካሄደበት ፊንላንድ ሄልሲንኪ እ.አ.አ በ2005 ነው። በሻምፒዮናው በ10 ሺህ ሜትር አትሌት ቀነኒሳ በቀለ ወርቅ፤ አትሌት ስለሺ ስህን የብር ሜዳሊያ አግኝተዋል። በ5 ሺህ ሜትር አትሌት ስለሺ ስህን የብር ሜዳሊያ አምጥቷል። በሴቶች በ5 ሺህ ሜትር አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ፣ መሰረት ደፋርና እጅጋየሁ ዲባባ ከአንድ እስከ ሶስት በመውጣት ኢትዮጵያን አኩርተዋል። በተመሳሳይ በሴቶች 10 ሺህ ሜትር አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ፣ ብርሃኔ አደሬና እጅግአየሁ ዲባባ ከ1ኛ እስከ ሶስተኛ በመውጣት ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው እንድትደምቅ አድርገዋታል። ጥሩነሽ ዲባባ በ5 ሺህና በ10 ሺህ ሜትር ወርቅ በማግኘት እንዲሁም እጅጋየሁ ዲባባ በተመሳሳይ ሁኔታ በ10 ሺህ እና በ5 ሺህ ርቀት በአንድ ውድድር ላይ ነሐስ በማምጣት በታሪክ የመጀመሪያዎቹ እህትማማቾች መሆን ችለዋል። 11ኛው ሻምፒዮና እ.አ.አ በ2007 በጃፓን ኦሳካ ናጋይ ስታዲየም ሲካሄድ አትሌት ቀነኒሳ በቀለና አትሌት ስለሺ ስህን በ10 ሺህ ሜትር የወርቅና ብር እንደዚሁም ጥሩነሽ ዲባባ ከሆድ ሕመሟ ጋር ታግላ በ10 ሺህ ሜትር ለሀገሯ ወርቅ መምጣት የቻለች ሲሆን በመሰረት ደፋር ደግሞ በ5 ሺህ ወርቅ ለማግኘት ተችሏል። ኢትዮጵያ በ4 ሜዳሊያ ከአለም 4ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። እ.አ.አ በ2009 በጀርመን በርሊን በተከናወነው 12ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በተለያዩ ርቀቶች የሚሳተፉ 38 አትሌቶችን ይዛ ቀርባለች፤ ቡድኑ በመካከለኛ ርቀት ጭምር የሚሳተፉ አትሌቶችን ያቀፈ ነበር። በሻምፒዮናው በወንዶች 5 ሺ ሜትርና 10 ሺ ሜትር ቀነኒሳ በቀለ ሁለት ወርቅ በማምጣት አዲስ ታሪክ የጻፈበት ክስተት ነበር። በ1 ሺህ 500 ሜትር ወንዶች ደረሰ መኮንን የብር ሜዳልያን ሲያሳካ፣ ፀጋዬ ከበደ በማራቶን ሁለተኛውን የብር ሜዳሊያ አስገኝቷል። በሴቶች በመሰረት ደፋር በ5000 ሜትር የነሐስ ሜዳልያ፣ መሰለች መልካሙ በ10 ሺህ ሜትር የብር እና ውዴ አያሌው የነሐስ፣ እንዲሁም አሰለፈች መርጊያ በማራቶን የነሐስ ሜዳሊያ አስገኝተዋል። ሻምፒዮናው ኢትዮጵያ በአጠቃላይ ስምንት ሜዳሊያ በመሰብሰብ ከዓለም ስድስተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀችበት ሆኖ አልፏል። እ.አ.አ በ2011 በኮሪያ ሪፐብሊክ ዴጉ ላይ በተካሄደው 13ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተካፈለው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ብሔራዊ ቡድን 34 አትሌቶች የተካከቱበት ነበር። በ10 ሺህ ሜትር ወንዶች አትሌት ኢብራሂም ጄይላን በመጨረሻው ዙር ፍጥነቱን በመጨመርና አስደናቂ የአጨራረስ ብቃቱን በመጠቀም ከኋላ ተነስቶ እንግሊዛዊውን አትሌት ሞ ፋራን ያሸነፈበት መንገድ አድናቆት ያስቸረውና ኢትዮጵያውያንን በደስታ ያስፈነጠዘ ነበር። በሻምፒዮናው አትሌት ደጀን ገብረ መስቀል በ5000 ሜትር፣ ኢማና መርጊያ በ10 ሺህ ሜትር፣ አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ በማራቶን እንዲሁም መሰረት ደፋር በ5000 ሜትር አራት የነሐስ ሜዳሊያዎች አስገኝተዋል። በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው አምስት ሜዳሊያዎችን በመሰብሰብ 10ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። እ.አ.አ በ2013 በሩሲያ ሞስኮ በተካሄደው 14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በመሰረት ደፋር በ5000 ሜትር ወርቅ፣ በጥሩነሽ ዲባባ 10 ሺህ ሜትር ወርቅ፣ እንዲሁም ለመጀመሪያ ጊዜ በ800 ሜትር ወንዶች በመሐመድ አማን ወርቅ ማምጣት ተችሏል። በሌሎች ርቀቶች ሶስት የብርና ሶስት የነሐስ ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ኢትዮጵያ ከዓለም ስድስተኛ ደረጃን በመያዝ ማጠናቀቅ ችላለች። እ.አ.አ በ2015 በቻይና ቤጂንግ በተካሄደው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ገንዘቤ ዲባባ በ1 ሺህ 500 ሜትር ወርቅ ማምጣት ችላ ነበር። በቤጂንጉ የዓለም ሻምፒዮና አትሌት አልማዝ አያና በ5000 ሜትር ወርቅና ማሬ ዲባባ በማራቶን ወርቅ ያገኙ ሲሆን ኢትዮጵያ በአጠቃላይ በአምስት ሜዳሊያዎች ከዓለም አምስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች፡፡ በ2017 በ16ኛው የለንደን ዓለም ሻምፒዮን አምስት ሜዳሊያዎች ኢትዮጵያ በማግኘት በዓለም ሰባተኛ ደረጃን ይዛ ተመልሳለች። ከሜዳሊያዎቹ ውስጥም በ5 ሺህ ሜትር በሙክታር እድሪስና በ10 ሺህ በአልማዝ አያና ሁለት የወርቅ ሜዳልያ ማግኘት ተችሏል፡፡ በ2019 የተካሄደው 17ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በኳታር ዶሃ የተደረገ ሲሆን ኢትዮጵያ በሁለት ወርቅና በአራት ብር በአጠቃላይ ስድስት ሜዳሊያዎች ማምጣት ችላለች። አትሌት ሙክታር እድሪስ በ5 ሺህ ሜትር ወንዶች በማሸነፍ በተከታታይ ሁለት ሻምፒዮናዎች በርቀቱ የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘት ችሏል። በማራቶን ደግሞ አትሌት ሌሊሳ ዴሲሳ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝቷል። በሻምፒዮናው አትሌት ለሜቻ ግርማ በ3000 መሰናክል የብር ሜዳሊያ አግኝቷል። ከዚያ በኋላ በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ሻምፒዮናው ለሁለት ዓመታት ሳይካሄድ ቆይቷል። እ.አ.አ. በ2022 ዓለም ከወረርሽኑ አገግማ በአሜሪካ ኦሬጎን በተካሄደው 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ቡድን ስኬታማውን የዓለም ሻምፒዮና ያገኘበት ውጤት አስመዘገበ። በሻምፒዮናው አትሌት ለተሰንበት ግደይ በ10 ሺህ ሜትር ሴቶች፣ አትሌት ጉዳፍ ጸጋይ በ5ሺህ ሜትር ሴቶች፣ አትሌት ጎይቲቶም ገብረስላሴ በሴቶች ማራቶን እና አትሌት ታምራት ቶላ በወንዶች ማራቶን የወርቅ ሜዳሊያ በማምጣት ኢትዮጵያን ያኮራ ድል አስመዘገቡ። አትሌት ጉዳፍ በ1 ሺህ 500 ሜትር ሴቶች የብር ሜዳሊያ በማግኘት በሻምፒዮናው ሁለት ሜዳሊያዎችን ማግኘት ችላለች። ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በማራቶን በሁለቱም ጾታ የሻምፒዮናውን ክብረ ወሰን ማሻሻል የቻሉ ሲሆን አትሌት ለተሰንበት በ10 ሺህ ሜትር የዓመቱን ምርጥ ሰዓት ማስመዝገብ ችላለች። ኢትዮጵያ በኦሬገኑ ዓለም ሻምፒዮን ከአራቱ ወርቅ በተጨማሪ አራት የብርና ሁለት የነሐስ በድምሩ 10 ሜዳልያዎችን በማግኘት ከዓለም ሁለተኛ ደረጃን ይዛ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ አጠናቃለች። የኦሬገኑ ውድድር ኢትዮጵያ በርካታ የወርቅ ሜዳሊያ ያገኘችበት ውድድርም ሆኖ አልፏል። ደማቅ ስኬት ላስመዘገበው የአትሌቲክስ ቡድን በአዲስ አበባ ደማቅ የጀግና አቀባበል የተደረገለት ሲሆን አትሌቶቹ በመዲናዋ አውራ ጎዳናዎች በመዘዋወር ከሕዝቡ ደስታውን በመግለጽ ድላቸውን አክብረዋል። ባሳለፍነው ሳምንት እ.አ.አ ከነሐሴ 19 እስከ 27 ቀን 2023 በሀንጋሪ ቡዳፔስት ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየም በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በ2 የወርቅ፣4 የብር እና በ3 የነሐስ በድምሩ ዘጠኝ ሜዳሊያዎችን በማግኘት ከዓለም ስድስተኛ ከአፍሪካ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቃለች። በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ በ34 አትሌቶች የተወከለች ሲሆን በሻምፒዮናው በ1 ሺህ 500፣ በ3 ሺህ ሜትር መሰናክል፣ በ5 ሺህ ሜትር፣ በ10 ሺህ ሜትርና በማራቶን በሁለቱም ጾታዎች እንዲሁም በ800 ሜትር በሴት ብቻ ተሳትፋለች። ኬንያ በ3 የወርቅ፣ በ3 የብር እና በ4 ነሐስ በድምሩ 10 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ከዓለም አምስተኛ ከአፍሪካ አንደኛ ደረጃን ይዛለች። አሜሪካ፣ ካናዳ፣ ስፔንና ጃማይካ በሜዳሊያ ሰንጠረዡ ከአንድ እስከ አራተኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል። በሻምፒዮናው መክፈቻ በ10 ሺህ ሜትር ሴቶች ፍጻሜ አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ፣ አትሌት ለተሰንበት ግደይና አትሌት እጅጋየሁ ታዬ ከአንድ እስከ ሶስት በመውጣት ያስመዘገቡት ድል ተጠቃሽ ነው። በሴቶች ማራቶን በአስገራሚ የቡድን ስራ አትሌት አማኔ በሪሶና አትሌት ጎይቲቶም ገብረስላሴ ያስገኙት የወርቅና የብር ሜዳሊያ የሚረሳ አይደለም። ኢትዮጵያ በተሳተፈችባቸው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች 35 የወርቅ፣ 38 የብር እና 31 የነሐስ ሜዳሊያዎችን በማግኘት በድምሩ 104 ሜዳሊያዎችን በማግኘት በሻምፒዮናው የምንጊዜም የሜዳሊያ ሰንጠረዥ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። 20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከመስከረም 3 እስከ 11 ቀን 2018 ዓ.ም በጃፓን ቶኪዮ ይካሄዳል።
ኢትዮጵያ በዓለም ሻምፒዮናው መክፈቻ ቡዳፔስት ላይ ወርቅ ባገኘችባቸው ርቀቶች የፍጻሜ ውድድሮች ይካሄዳሉ
Sep 13, 2025 71
አዲስ አበባ፤ መስከረም 3/2018 (ኢዜአ)፦ በጃፓን ቶኪዮ የሚካሄደው 20ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ይጀመራል። በሻምፒዮናው መክፈቻ ቀን ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ በሚደረገው የሴቶች የ10 ሺህ ሜትር የፍጻሜ ውድድር ጉዳፍ ጸጋይ፣ ፅጌ ገብረሰላማ፣ ፎይተን ተስፋይ እና እጅጋየሁ ታዬ ይወዳደራሉ። ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት በሴቶች ማራቶን አትሌት ትዕግስት አሰፋ፣ ሱቱሜ አሰፋ እና ትዕግስት ከተማ ኢትዮጵያን ወክለው ይሳተፋሉ። ኢትዮጵያ በሁለቱም ወድድሮች እ.አ.አ በ2019 በሀንጋሪ በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ በ10 ሺህ ሜትር ለኢትዮጵያ የወርቅ ሜዳሊያ አስገኝታ የነበረ ሲሆን ይህም ውጤቷ ጉዳፍ በዛሬው ውድድር ላይ ያለ ማጣሪያ በቀጥታ እንድትሳተፍ አስችሏታል። በ19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በሴቶች ማራቶን በአትሌት አማኔ በሪሶ አማካኝነት ኢትዮጵያ የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘቷ የሚታወስ ነው። አትሌት አማኔ በህመም ምክንያት በዛሬው ውድድር ላይ ባትሳተፍም ሌሎች ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የማራቶኑን ክብር ለማስጠበቅ ይሮጣሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም