ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ነጌሌ አርሲ በኢትዮጵያ ዋንጫ ለሩብ ፍጻሜ ያለፈ የመጀመሪያው ክለብ ሆኗል
Dec 13, 2025 39
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር ዛሬ ተጀምሯል። ረፋድ ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው የመጀመሪያ ጨዋታ ነጌሌ አርሲ አቃቂ ክፍለ ከተማን 4 ለ 0 አሸንፏል። ርሆቦት ሰላሎ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አለኝታ ማርቆስ እና ሀቢብ ከማል ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ነጌሌ አርሲ በኢትዮጵያ ዋንጫ ለሩብ ፍጻሜ ያለፈ የመጀመሪያው ክለብ ሆኗል። የኢትዮጵያ ዋንጫ የመጀመሪያ ቀን ቀሪ ጨዋታዎች ከቀትር በኋላ ይካሄዳሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ቦሌ ክፍለ ከተማ እና ሃዋሳ ከተማ ነጥብ ተጋርተዋል
Dec 13, 2025 38
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ቦሌ ክፍለ ከተማ እና ሃዋሳ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ጨዋታው ረፋድ ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ተካሄዷል። ሃዋሳ ከተማ በ26 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ20 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ከቀኑ 7 ሰዓት አዲስ አበባ ከተማ ከመቻል በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ብሄራዊ ምልክት የሆነው አንጋፋው የኢትዮጵያ ዋንጫ ውድድር
Dec 13, 2025 40
የኢትዮጵያ ዋንጫ በ1937 ዓ.ም የተጀመረ አንጋፋ የጥሎ ማለፍ ውድድር ነው። ውድድሩ በወቅቱ የነበረውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር (አሁን የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ) ለመደገፍ ነበር። የጥሎ ማለፍ ውድድር ፎርማት የሆነው የኢትዮጵያ ዋንጫ እንደ እንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ እና በሌሎች ሀገራት ከሚደረጉ ውድድሮች ተመሳሳይነት ያለው ነው። በውድድሩ የመጀመሪያ ዓመታት ላይ ይሳተፉ የነበሩ ክለቦች በአዲስ አበባ እና ዙሪያ የሚገኙ ክለቦች ናቸው። የእግር ኳስ መዋቅሮችን ለመዘርጋት እና ሀገር በቀል አቅምን ለመለየት የመጀመሪያ ዓመታት ውድድሮች ወሳኝ ሚና ነበራቸው። በኢትዮጵያ አቆጣጠር 1950ዎቹ እና 1960ዎቹ ላይ የኢትዮጵያ ዋንጫ በጊዜ ሂደት እየሰፋ በመምጣት ብሄራዊ እውቅናን ያገኘ ሲሆን በተለያዩ የሀገሪቷ ክፍሎች የሚገኙ ክለቦች በስፋት መሳተፍ ጀመሩ። ውድድሩ የብሄራዊ አንድነት መገለጫ እና መሳሪያ መሆንም ችሏል። የእግር ኳስ መሰረተ ልማት እያደገ መምጣት በተለይም የስታዲየሞች እና የልምምድ ስፍራዎች መስፋት የሊግ ውድድሮች ለኢትዮጵያ ዋንጫ እድገት የበኩላቸውን ሚና ተጫውተዋል። በታህሳስ ወር 1928 ዓ.ም የተመሰረተው የመጀመሪያው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ክለብ ቅዱስ ጊዮርጊስ ውድድሩን ለበርካታ ጊዜያት በማንሳት የበላይነቱን ይዟል። ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1970ዎች እና በ1980 ዎቹ የመንግስት እና የንግድ ድርጅቶች መሳተፍ የጀመሩበት ወቅት ነው። ኢትዮጵያ ቡና፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ (በድሮ አጠራሩ መብራት ሃይል)፣ እርሻ ሰብል፣ ኢትዮ ሲሚንቶ፣ መቻል እና ኢትዮጵያ መድን ከተሳታፊዎቹ መካከል ይጠቀሳሉ። 1970ዎች እና በ1980ዎቹ የኢትዮጵያ ዋንጫ ውድድር የበለጠ ቅርጽ እየያዘ እና እየተዋቀረ የመጣበት ወቅት ነው። የመርሃ ግብሮች የጊዜ ሰሌዳ፣ ሽልማት ክፍፍል እና የዳኝነት አሰራሩ መሻሻል ያሳየበት ነው። የመገናኛ ብዙሃን የዘገባ ሽፋን መስፋትም ውድድሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ ቁልፍ ስፖርታዊ ሁነት እንዲሆን አስችሎታል። በኢትዮጵያ በ1980ዎቹ መጀመሪያ ላይ የኢትዮጵያ ዋንጫ ከካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ (ካፍ) ውድድሮች ጋር በማስተሳሰር ክለቦች በአህጉር አቀፍ ደረጃ የመሳተፍ እድል እንዲያገኙ አስችሏል። በ199ዎቹ እና በኢትዮጵያ ሚሊኒየም ከሁለት ሺህ በኋላ የኢትዮጵያ ዋንጫ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የስፖርት አፍቃሪ በስታዲየም ገብቶ የሚመለከተው እና ሰፊ የሚዲያ ሽፋን ያገኘ ሆኗል። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሚያሸንፉ ቡድኖች የካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ተሳታፊ በመሆን ይሳተፋሉ። የኢትዮጵያ ዋንጫ በተለያዩ ምክንያቶች በተለያዩ ጊዜያት ተቋርጦ የነበረ ቢሆንም አሁንም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ምልክት ሆኖ ቀጥሏል። ውድድሩ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ባህል እና እድገት መለኪያ መሆን የቻለ ሲሆን በዜጎች መካከል የእርስ በእርስ ትብብርን በመፍጠር ረገድ የበኩሉን ሚና ተወጥቷል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ሲነሳ የኢትዮጵያ ዋንጫን አለማንሳት አይቻልም። መቻል እና ቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያን ዋንጫ በብዛት ማንሳት ስኬታማው ክለብ ናቸው። ኢትዮ ኤሌክትሪክ፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ፣ እርሻ ሰብል፣ አዳማ ከተማ፣ ኢትዮጵያ ቡና፣ ሲዳማ ቡና፣ ሃዋሳ ከተማ እና ወላይታ ድቻ ሌሎች የኢትዮጵያ ዋንጫን ካነሱ ክለቦች መካከል ይጠቀሳሉ። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር ከታህሳስ 4 እስከ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ቅዳሜ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ከነጌሌ አርሲ ከረፋዱ አራት ሰዓት፣ ባህር ዳር ከተማ ከቦዲቲ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ኢትዮጵያ መድን ከቢሾፍቱ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየም መቻል ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። መርሃ ግብሩ እሁድም ቀጥሎ ሲውል ደብረ ብርሃን ከተማ ከቤንች ማጂ ቡና በአዲስ አበባ ስታዲየም እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከንብ እግር ኳስ ክለብ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተመሳሳይ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና ከአርባ ምንጭ ከተማ በአዲስ አበባ አበባ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ ። ሰኞ ታህሳስ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ኢትዮጵያ ቡና ከመቀሌ 70 እንደርታ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሶስተኛው ዙር የሚያሸንፉ ክለቦች ለሩብ ፍጻሜ ያልፋሉ። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ በአንደኛው ዙር መሰናበቱ የሚታወስ ነው። የኢትዮጵያ ዋንጫን የሚያሸንፈው ቡድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል።
የሊጉ መሪ አርሰናል ከዎልቭስ ጋር ይጫወታል
Dec 13, 2025 67
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ):- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። ምሽት አምስት ሰዓት ላይ አርሰናል ዎልቭስን በኤምሬትስ ስታዲየም ያስተናግዳል። አርሰናል ሊጉን በ33 ነጥብ እየመራ ሲሆን ዎልቭስ በሁለት ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። አርሰናል በውድድር ዓመቱ ባደረጋቸው 15 ጨዋታዎች በ10ሩ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፎ በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። አርሰናል ባከናወናቸው በጨዋታዎች 28 ግቦችን ሲያስቆጥር ዘጠኝ ግቦች አስተናግዷል። ተጋጣሚው ዎልቭስ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ አላሸነፈም። በ13ቱ ሲሸነፍ ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። ባከናወናቸው 15 ጨዋታዎች ስምንት ጎሎችን ሲያስቆጥር 33 ግቦች ተቆጥረውበታል። አርሰናል በ15ኛ ሳምንት በአስቶንቪላ ከደረሰበት ሽንፈት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በፕሪሚየር ሊጉ መጥፎ የውድድር ዓመት እያሳለፈ የሚገኘው ዎልቭስ በሊጉ የመጀመሪያ ሶስት ነጥቡን ለማግኘት ከባድ ፈተና ይጠብቀዋል። አርሰናል ጨዋታውን የማሸነፍ ሰፊ ግምት ያገኘ ሲሆን ካሸነፈ ከተከታያቸው ማንችስተር ሲቲ ጋር ያላቸውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ ያደርጋሉ። የ38 ዓመቱ ሮበርት ጆንስ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ቼልሲ ከኤቨርተን እና ሊቨርፑል ከብራይተን በተመሳሳይ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በርንሌይ ከፉልሃም ምሽት 2 ሰዓት 30 ላይ ይጫወታሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ የሚደረጉ ጨዋታዎች
Dec 13, 2025 53
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ቦሌ ክፍለ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቦሌ ክፍለ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 11 ጨዋታዎች አምስቱን ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። አራት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 13 ግቦችን ሲያስቆጥር 11 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ19 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሃዋሳ ከተማ 11 ጨዋታዎችን አድርጎ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። 22 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ዘጠኝ ግቦች ተቆጥረውበታል። ሃዋሳ ከተማ በ25 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኖቹ በአሸናፊነት ጉዟቸው ለመቀጠል የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ11ኛ ሳምንት ጨዋታ የሊጉን መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር አዲስ አበባ ከተማ ከመቻል ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው 11 ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ስምንት ጊዜ ሲሸነፍ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 22 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃ ይዟል። በሊጉ ካከናወናቸው 11 ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ያሸነፈው መቻል ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 18 ግቦችን በ11ዱ ጨዋታዎች ላይ ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። መቻል በ23 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ሁለተኛ ድሉን ለማስመዝገብ፣ መቻል ወደ መሪዎቹ መጠጋት የሚያስችለውን ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል
Dec 13, 2025 65
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር የመጀመሪያ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ከነጌሌ አርሲ ከረፋዱ አራት ሰዓት፣ ባህር ዳር ከተማ ከቦዲቲ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ኢትዮጵያ መድን ከቢሾፍቱ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየም መቻል ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር እስከ ታህሳስ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ በአንደኛው ዙር ዙር መሰናበቱ የሚታወስ ነው። የኢትዮጵያ ዋንጫን የሚያሸንፈው ቡድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል። የኢትዮጵያ ዋንጫ በ1937 ዓ.ም የተጀመረ አንጋፋ የጥሎ ማለፍ ውድድር ነው።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሸገር ከተማ ደረጃውን ወደ አራተኛ ከፍ ያደረገበትን ድል አስመዘገበ
Dec 12, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሸገር ከተማ ይርጋ ጨፌ ቡናን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው አይናለም አለማየሁ እና ሰናይት ኡራጎ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ድሉን ያስመዘገበው ሸገር ከተማ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ24 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ይርጋ ጨፌ ቡና በ10 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረጉ የ12ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ሲዳማ ቡና አርባ ምንጭ ከተማን፣ ባህር ዳር ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ወጣቶች ጨዋታዎች ሶስተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
Dec 12, 2025 87
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ በአንጎላ ሉዋንዳ እየተካሄደ የሚገኘው አራተኛው የአፍሪካ ወጣቶች ጨዋታዎች ዛሬ ሶስተኛ ቀኑን ይዟል። የሴቶች ብስክሌት የግል ሰዓት ሙከራ ውድድር ማህደር ደስታ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። ከሁለተኛው የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ወጣቶች ጨዋታዎች የተገኘችው ማህደር ያገኘችው ወርቅ በውድድሩ ለኢትዮጵያ ሶስተኛ የወርቅ ሜዳሊያ ሆኖ መመዝገቡን የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ኢትዮጵያ በ3000 ሜትር ሴቶች እና በሴቶች ብስክሌት የቡድን የሰዓት ሙከራ የወርቅ ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። ኢትዮጵያ በውድድሩ ላይ በሁለቱም ጾታዎች በሰባት የስፖርት አይነቶች 70 ስፖርተኞችን እያሳተፈች ይገኛል። አትሌቲክስ፣ ብስክሌት፣ ወርልድ ቴኳንዶ፣ ካራቴ፣ ጠረጴዛ ቴኒስ፣ ውሃ ዋና እና ክብደት ማንሳት ኢትዮጵያ የምትሳተፍባቸው የስፖርት አይነቶች ናቸው። በአፍሪካ ወጣቶች ጨዋታዎች ላይ እየተሳተፉ የሚገኙ ስፖርተኞች በቅርቡ በተካሄደው ሁለተኛው የኢትዮጵያ የኦሎምፒክ ጨዋታዎች ላይ ባስመዘገቡት ውጤት የተመረጡ መሆናቸው ይታወቃል። በውድድሩ ላይ 54 ሀገራት በ33 የስፖርት አይነቶች እየተሳተፉ ነው። አህጉራዊው የስፖርት ሁነት እስከ ታህሳስ 16 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የአፍሪካ ወጣቶች ጨዋታዎች በ2019 ዓ.ም በሴኔጋል ዳካር ለሚካሄደው አራተኛው የወጣቶች የክረምት ኦሊምፒክ እንደ ማጣሪያ እና መዘጋጃ የሚያገለገል ውድድር ነው።
ባህር ዳር ከተማ በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ድሉን በማስመዝገብ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል
Dec 12, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አስቴር ይርጋ በ15ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። በሊጉ ሁለተኛ ድሉን ያስመዘገበው ባህር ዳር ከተማ በሰባት ነጥብ ደረጃውን ከ14ኛ ወደ 12ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ልደታ ክፍለ ከተማ በአምስት ነጥብ ደረጃውን ከ12ኛ ወደ 13ኛ ዝቅ በማለት ወራጅ ቀጠና ውስጥ ገብቷል። በአሁኑ ሰዓት ይርጋ ጨፌ ቡና ከሸገር ከተማ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሲዳማ ቡና አርባ ምንጭ ከተማን አሸነፈ
Dec 12, 2025 78
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ሲዳማ ቡና አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአርባ ምንጭ ከተማዋ አረጋሽ ፀጋ በ14ኛው ደቂቃ በራሷ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። በሊጉ አራተኛ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በ15 ነጥብ ደረጃውን ከስምንተኛ ወደ ሰባተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በስምንት ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል
Dec 12, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይደረጋሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከሲዳማ ቡና ይጫወታሉ። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ በሊጉ ካከናወናቸው 11 ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን ሲያሸንፍ ሰባት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ሰባት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 20 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በስምንት ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና እስከ አሁን በሊጉ ባካሄዳቸው 10 ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ በአራቱ ተሸንፏል። በሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። አራት ግቦችን በነዚህ ጨዋታዎች ከመረብ ላይ ሲያገናኝ 11 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሲዳማ ቡና አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ12 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከልደታ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው 11 ጨዋታዎች መካከል አንዱን ብቻ ያሸነፈው ባህር ዳር ከተማ በዘጠኝ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። አንድ ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 16 ጎሎችን አስተናግዷል። ባህር ዳር ከተማ በአራት ነጥብ የመጨረሻውን 14ተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ልደታ ክፍለ ከተማ በሊጉ 11 ጨዋታዎችን አድርጎ አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ ስምንት ጊዜ ተሸንፏል። ሁለት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ስምንት ግቦችን ሲያስቆጥር 22 ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የዕለቱ የመጨረሻ መርሃ ግብር አዲስ አዳጊዎቹ ይርጋጨፌ ቡና እና ሸገር ከተማን ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ያገናኛል። ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው 11 ጨዋታዎች በሁለቱ ተሸንፎ በአምስቱ ተሸንፎ በአራቱ አቻ ወጥቷል። አራት ግቦችን ሲያስቆጥር 13 ግቦችን እሰተናግዷል። ቡድኑ በ10 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሸገር ከተማ በሊጉ ባከናወናቸው 10 ጨዋታዎች ሰባቱን ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። በጨዋታዎቹ ላይ 16 ግቦችን ሲያስቆጥር 10 ግቦችን አስተናግዷል። ሸገር ከተማ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ21 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
የመጀመሪያው የኢትዮጵያ የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር በመቀሌ ይካሄዳል
Dec 11, 2025 118
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 2/2018 (ኢዜአ)፦ የመጀመሪያው የኢትዮጵያ የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር እሁድ ታህሳስ 5 ቀን 2018 በመቀሌ ከተማ እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታወቀ። የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኑ የውድድሩን ዝግጅት አስመልክቶ ዛሬ በሰጠው መግለጫ ፤ በጎዳና ላይ ሩጫው በአጠቃላይ 79 አትሌቶች ለመወዳደር መመዝገባቸውን ገልጿል። ውድድሩ ለክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች፣ ክለቦች ፣ተቋማት፣ የግል ተወዳዳሪ አትሌቶች የውድድር ዕድል ለመፍጠር ፣ ተተኪ አትሌቶችን ማፍራት እና አትሌቶችን በሽልማት ማበረታትን አላማ ያደረገ መሆኑ ተመላክቷል። 40 ዳኞች ውድድሩን እንዲመሩ መመደባቸውንና ለአሸናፊ አትሌቶች ሽልማት መዘጋጀቱ በመግለጫው ላይ ተነስቷል። የአትሌቶች ምዝገባ እስከ ነገ ድረስ እንደሚቀጥል እና ያልተመዘገቡ ተወዳዳሪዎች እንዲመዘገቡም ፌዴሬሽኑ ጥሪ አቅርቧል።
የባህል ስፖርት ውድድሮች የህብረተሰቡን እሴቶች ለማስተዋወቅ ተጨማሪ አቅም ይፈጥራሉ
Dec 11, 2025 94
ጅማ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ የባህል ስፖርታዊ ውድድሮች የህብረተሰቡን እሴቶች በማስተዋወቅ ተጨማሪ አቅም እንደሚፈጥሩ የጅማ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ቲጃኒ ናስር ገለጹ። የጅማ ዞን የወረዳዎች የባህል ስፖርት ውድድርና እና ኤግዚቢሽን መርሀ ግብር ዛሬ መካሄድ ጀመረ። በመክፈቻ መርሀግብሩ ላይ የተገኙት የጅማ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ቲጃኒ ናስር እንዳሉት፤ በዞን ደረጃ የሚካሄደው የባህል ስፖርት ውድድርና የባህል ኤግዚቢሽን ማህበረሰባዊ እሴቶችን ሳይበረዙ ለትውልዱ ለማስተላለፍ መደላድል ፈጥሯል። ስፖርታዊ ውድድሩ የህብረተሰቡን ባህላዊ እሴቶች በማስተዋወቅ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳቸውን ለማጉላት እንደሚያግዝም ጠቁመዋል። በዞኑ ያሉትን የባህል እሴቶች ለማህበረሰባዊ ትስስር ለማዋል መሰል ኤግዚቢሽኖች ጠቀሜታቸው የጎላ መሆኑን አክለዋል። የጅማ ዞን ስፖርት ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ነጉማ መኮንን በበኩላቸው፤ የባህል ስፖርት ውድድር የስፖርቱን ዘርፍ ወንድማማችነትና እህትማማችነት የሚያጠናክር መሆኑን ጠቁመዋል። ለ13 ቀናት በሚካሄደው የባህል ስፖርት ውድድሩ ከ20 ወረዳዎችና ከአንድ ከተማ አስተዳደር የተውጣጡ የባህል ስፖርት ተወዳዳሪዎችና የባህል ቡድኖች እንደሚሳተፉ ተናግረዋል። በአስር የባህል የስፖርት አይነቶች ውድድር የሚደረግ መሆኑን ገልጸው የፈረስ ግልቢያ፣ የገበጣ፣ቀስት፣ ትግል እና የገና ጨዋታ ስፖርቶች ይገኙባቸዋል ብለዋል።
በተጠባቂው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ሪያል ማድሪድን አሸነፈ
Dec 11, 2025 135
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሊግ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጠባቂ መርሃ ግብ ማንችስተር ሲቲ ሪያል ማድሪድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በሳንቲያጎ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኒኮ ኦራይሊ በጨዋታ እና አርሊንግ ሃላንድ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሮድሪጎ ለሪያል ማድሪድ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ላይ ማንችስተር ሲቲ በመጀመሪያው አጋማሽ እና ሪያል ማድሪድ በሁለተኛው አጋማሽ ብልጫ ወስደው ተጫውተዋል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ በ13 ነጥብ ደረጃውን ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። የ15 ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሪያል ማድሪድ በ12 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። አርሊንግ ሃላንድ በሻምፒዮንስ ሊግ በ50 ጨዋታዎች 51 ግቦችን ያስቆጠረ የመጀመሪያው ተጫዋች በመሆን አዲስ ክብረ ወሰን አስመዝግቧል። በሌላኛው መርሃ ግብር አርሰናል ክለብ ብሩዥን 3 ለ 0 አሸንፏል። በጃን ብሬይዴል ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኖኒ ማዱዌኬ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ጋብርኤል ማርቲኔሊ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። አርሰናል በ18 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። መድፈኞቹ በሻምፒዮንስ ሊግ ሁሉንም ጨዋታ ማሸነፍ ችለዋል። ክለብ ብሩዥ በአራት ነጥብ 31ኛ ደረጃን ይዟል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ ከአትሌቲኮ ቢልባኦ ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ጁቬንቱስ በጆናታን ዴቪድ እና ዌስተን ማኬኒ ግቦች ፓፎስን 2 ለ ዐ አሸንፏል። ቤኔፊካ ናፖሊን 2 ለ 0 አሸንፏል። ባየር ሌቨርኩሰን ከኒውካስትል ዩናይትድ እና ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ከቦዶ ግሊምት በተመሳሳይ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች አያክስ ካራባግን 4 ለ 2፣ ኮፐንሃገን ቪያሪያልን 3 ለ 2 አሸንፈዋል።
በሊጉ ተስተካካይ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ መድን ሸገር ከተማን አሸነፈ
Dec 10, 2025 127
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት ተስተካካይ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን ሸገር ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አማኑኤል ኤርቦ በ48ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ድሉን ያስመዘገበው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ12 ነጥብ ደረጃውን ከ14ኛ ወደ 12ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በሊጉ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በተመሳሳይ 12 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ በ12 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። መርሃ ግብሩ ኢትዮጵያ መድን በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ከግብጹ ፒራሚድስ ጋር በነበረው የማጣሪያ ጨዋታ ምክንያት የተራዘመ መሆኑን የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
ኢትዮጵያ መድን ከሸገር ከተማ ጋር ተስተካካይ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል
Dec 10, 2025 118
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ መድን ከሸገር ከተማ ይጫወታሉ። ጨዋታው ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ መድን በሊጉ ካደረጋቸው ስምንት ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን ሲያሽንፍ ሶስት ጊዜ ደግሞ ተሸንፏል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ጎሎችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በዘጠኝ ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ሸገር ከተማ በበኩሉ በሊጉ ካከናወናቸው ስምንት ጨዋታዎች መካከል በሶስቱ ድል ሲቀናው ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። ሶስት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያገናኝ ሰባት ግቦች ተቆጥረውበታል። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በ12 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው ኢትዮጵያ መድን ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ሸገር ከተማ ደግሞ በአሸናፊነቱ ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው። መርሃ ግብሩ ኢትዮጵያ መድን በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ከግብጹ ፒራሚድስ ጋር በነበረው የማጣሪያ ጨዋታ ምክንያት የተራዘመ መሆኑን የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
ተጠባቂው የሪያል ማድሪድ እና የማንችስተር ሲቲ የሻምፒዮንስ ሊግ ፍልሚያ
Dec 10, 2025 116
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፡- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዛሬ ዘጠኝ ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 5 ሰዓት ላይ ሪያል ማድሪድ እና ማንችስተር በበርናባው ስታዲየም የሚያገናኘው ጨዋታ የእግር ኳስ ቤተሰቡን ትኩረት ስቧል። ሪያል ማድሪድ በ12 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ማንችስተር ሲቲ በ10 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ15ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 14 ጨዋታዎች ማንችስተር ሲቲ አምስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሪያል ማድሪድ አራት ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ሁለቱም ቡድኖች በጨዋታዎቹ ላይ በተመሳሳይ 24 ግቦችን አስቆጥረዋል። ቡድኖቹ በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ2024/25 የውድድር ዓመት ነው። በጥሎ ማለፉ ተገናኝተው ሪያል ማድሪድ ማንችስተር ሲቲን 3 ለ 1 አሸንፏል። የስፔኑ ቡድን 15 ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ በስኬት ያሸበረቀ ታሪክ አለው። ማንችስተር ሲቲ አንድ ጊዜ ዋንጫ አንስቷል። ሪያል ማድሪድ እና ማንችስተር ሲቲ ባለፉት ዓመታት በአውሮፓ መድረክ እያደረጉት ያለው ፉክክር የዛሬውን ጨዋታ ትኩረት እንዲያገኝ አድርጎታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ክለብ ብሩዥ ከሊግ ፎርማቱ መሪ አርሰናል፣ አትሌቲኮ ቢልባኦ ከወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ፒኤስጂ፣ ጁቬንቱስ ከፓፎስ፣ ቤኔፊካ ከናፖሊ፣ ባየር ሌቨርኩሰን ከኒውካስትል ዩናይትድ እና ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ከቦዶ ግሊምት በተመሳሳይ ከምሽቱ 5 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ45 ካራባግ ከአያክስ እና ቪያሪያል ከኮፐንሃገን ይጫወታሉ።
ሊቨርፑል ኢንተር ሚላንን አሸነፈ
Dec 10, 2025 116
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሊግ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጠባቂ ጨዋታ ሊቨርፑል ኢንተር ሚላንን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በጁሴፔ ሜኤዛ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዶምኒክ ስቦዝላይ በ88ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት አስቆጥሯል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቱን ተከትሎ ሊቨርፑል በ12 ነጥብ ደረጃውን ወደ ስምንት ከፍ አድርጓል። ኢንተር ሚላን በተመሳሳይ 12 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በሌላኛው ጨዋታ አትላንታ ቼልሲን 2 ለ 1 አሸንፏል። ጂያንሉካ ስካማካ እና ቻርልስ ዲ ኬቴላሬ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጆአኦ ፔድሮ ለቼልሲ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ ስላቪያ ፕራግን 3 ለ 0 አሸንፏል። መሐመድ ኩዱስ፣ ዣቪ ሲመንስ እና የስላቪያ ፕራጉ ዴቫድ ዚማ በራሱ ላይ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ጁል ኩንዴ ባስቆጠራቸው ግቦች ባርሴሎና ከመመራት ተነስቶ ኢንትራክት ፍራንክፈርትን 2 ለ 1 አሸንፏል። አንስጋር ናውፍ ለጀርመኑ ቡድን ብቸኛውን ጎል ከመረብ ጋር አገናኝቷል። በሌሎች ጨዋታዎች አትሌቲኮ ማድሪድ ፒኤስቪ አይንድሆቨንን እና ማርሴይ ዩኒየን ሴንት ጊሎይስን በተመሳሳይ 3 ለ 2 ሲያሸንፉ ሞናኮ ጋላታሳራይን 1 ለ 0 ረቷል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ባየር ሙኒክ ስፖርቲንግ ሊዝበንን 3 ለ 1፣ ኦሎምፒያኮስ ካይራት አልማቲን 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
ባየር ሙኒክ ስፖርቲንግ ሊዝበንን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Dec 10, 2025 82
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ የአውሮፓ ሊግ ሻምፒዮንስ ሊግ የስድስተኛ ጨዋታ መርሃ ግብር ዛሬ ማምሻውን ተጀምሯል። በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ባየር ሙኒክ ስፖርቲንግ ሊዝበንን 3 ለ 1 አሸንፏል። ሰርጌ ናብሪ፣ ሌናርት ካርል እና ጆናታን ታህ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የባየር ሙኒኩ ተከላካይ ጆሹዋ ኪሚች በራሱ ላይ ለስፖርቲንግ ግቧን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በውድድሩ አምስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ባየር ሙኒክ በ15 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ ሁለተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ስፖርቲንግ ሊዝበን በ10 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሃ ግብር ኦሎምፒያኮስ ካይራት አልማቲን በጌልሰን ማርቲንስ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል።
የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ሽንፈቱን አስተናገደ
Dec 9, 2025 97
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 30/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ቦሌ ክፍለ ከተማ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳሳሽ ሰውአገኝ እና ሚሊዮን ጋይም የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዳግማዊት ሰለሞን ለኢትዮ ኤሌክትሪክ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ያለመሸነፍ ጉዞ 11ኛ ሳምንት ላይ ተገቷል። ቡድኑ 30 ነጥብ ላይ ረግቷል። በአንጻሩ በሊጉ አምስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ19 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ አጥቂ ዳግማዊት ሰለሞን በውድድር ዓመቱ ያስቆጠረቻቸውን ግቦች ወደ 17 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቷን አጠናክራለች። ዛሬ በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድሬዳዋ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ11ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ12ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከታህሳስ 3 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እንደሚካሄዱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።