ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የታዳጊ ህጻናት የእግር ኳስ ፕሮጀክት ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት በማለም ስልጠና እየሰጠ ነው
Mar 18, 2024 398
ሀዋሳ ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የታዳጊ ህጻናት የእግር ኳስ ፕሮጀክት ኢትዮጵያን ብሎም ክልሉን የሚተኩ ስፖርተኞችን ለማፍራት አልሞ በእግር ኳሱ ዘርፍ የሚጠበቅበትን ሀገራዊ ድርሻ ለመወጣት እየሰራ መሆኑን ገለጸ። የዩኒቨርሲቲው የስልጠና ፕሮጀክት በአሁኑ ወቅት ዕድሜያቸው ከ13ና ከ15 ዓመት በታች የሆኑ ከ60 በላይ ታዳጊ ህጻናትን በመቀበል በእግር ኳስ ስፖርት እያሰለጠነ ይገኛል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የስፖርት ሳይንስ ትምህርት ክፍል ረዳት ኃላፊ ፕሮፌሰር አንዷለም ገብረስላሴ እንዳሉት፤ ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ስራው ባሻገር በማህበረሰብ አገልግሎት በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ነው። ከዚህ ውስጥ አንዱ የስፖርቱ ዘርፍ ሲሆን ተተኪና ተወዳዳሪ ስፖርተኞችን በማፍራት የሚጠበቅበትን አስተዋጽኦ ለማበርከት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተለይም በእግር ኳስ እንደ ሀገር የሚጠበቅበትን ለመወጣት የታዳጊ ህጻናት ፕሮጀክት በመክፈት በአካባቢው አቅሙና ፍላጎቱ ያላቸውን ታዳጊዎች በግልጽ ውድድር በመቀበል እያሰለጠነ እንደሚገኝ ተናግረዋል ። መደበኛ ተማሪዎችም በአካል ብቃትና በአዕምሮ ዳብረው አምራች ዜጋ ሆነው እንዲወጡ ለማስቻል ዩኒቨርሲቲው አበክሮ እየሰራ ነው ብለዋል። በስፖርቱ ዘርፍ በተለይም በርካታ ደጋፊ ባለውና ተወዳጅ በሆነው በእግር ኳስ ዘርፍ ተፎካካሪ ለመሆን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት አስተዋጽኦን ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል ። አካባቢው ካለው እምቅ የእግር ኳስ አቅም አንጻር ለሀገር የሚተርፉ ተጨዋቾችን ለማፍራት ታሳቢ ተደርጎ ፕሮጀክት ተቀርጾ ወደ ስራ መገባቱን የተናገሩት ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የስፖርት ሳይንስ መምህርና ከ15 ዓመት በታች የእግር ኳስ ፕሮጀክት አሰልጣኝ ወንድወሰን ታዬ ናቸው። ባለፉት ሁለት ዓመታት በተደረገ ጥረት ከ60 በላይ ዕድሜያቸው ከ13ና ከ15 ዓመት በታች የሆኑ ታዳጊ ህፃናትን ይዘው በዩኒቨርሲቲው ሜዳና የስፖርት ግብአት እያሰለጠኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በዩኒቨርሲቲው ፕሮጀክት የሰለጠኑ ልጆችን ወደ ሀዋሳ ከነማ እግር ኳስ ክለብና ወደ ሌሎች ክለቦች እንዲገቡ መደረጉን ተናግረው የስፖርቱ ዘርፍ የማህበረሰብ አገልግሎት አካል ሆኖ እንዲጠናከር እየተሰራ ነው ብለዋል። ሌላኛው የስፖርት ሳይንስ ክፍል መምህርና ከ13 ዓመት በታች ፕሮጀክት አሰልጣኝ አለማየሁ አሻንጎ በበኩላቸው የእግር ኳስ ዕድገት ከታሰበ በታዳጊዎች ላይ መሰራት እንዳለበት ገልጸው በዚህ ረገድ ታዳጊዎችን በመመልመል እያሰለጠንን እንገኛለን ብለዋል። በዚህ ዕድሜ ስልጠና የሚወስዱ ልጆች ለሀገር ኩራት እስከመሆን ሊደርሱ እንደሚችሉ ያላቸውንም ዕምነት ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው ከ17 ዓመት በታች ፕሮጀክት በመታቀፍ እየሰለጠነ የሚገኘውና የ11ኛ ክፍል ተማሪው ብሩክ ዮሐንስ ባገኘው ዕድል ደስተኛ መሆኑን ተናግሮ ስፖርቱን ለማሳደግ በታዳጊዎች ላይ መስራት ወሳኝ መሆኑን ተነግሯል። በዩኒቨርሲቲው የሚሰጣቸው ስልጠና ከሜዳ አጠቃቀምና ሌሎች ቴክኒካል ጉዳዮች አንጻር ሳይንሳዊ መሰረት ያለው መሆኑን ጠቅሶ በቀጣይ በትልቅ ደረጃ ለመጫወት ማቀዱንም ገልጿል። በዩኒቨርሲቲው ፕሮጀክት ከ15 ዓመት በታች እየሰለጠነ የሚገኘው ታዳጊ ኤቤል አባተ በበኩሉ የ8ኛ ክፍል ተማሪ ሲሆን በዩኒቨርሲቲው ባገኘው የስልጠና ዕድል ችሎታውን እያሻሻለ መሆኑን ገልጿል።
በስፔን የ10 ሺ ሜትር ውድድር አትሌት ዮሚፍ ቀጄልቻ አሸነፈ
Mar 17, 2024 127
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦ በስፔን ላሬዶ በተካሄደው የ10 ሺ ሜትር ሩጫ ውድድር አትሌት ዮሚፍ ቀጄልቻ ርቀቱን 26 ደቂቃ ከ36 ሰከንድ በሆነ ሰዓት በመግባት አሸንፏል፡፡ አትሌት ዮሚፍ ቀጄልቻ ውድድሩን የጨረሰበት ሰዓት የርቀቱ የምንግዜም ሶስተኛው ፈጣን ሰዓት ተብሎ ተመዝግቧል፡፡ አትሌቱ ውድድሩን ያሸነፈው የ5ሺ እና የ10ሺ ሜትር የሪከርድ ባለቤቱንና አሸናፊ ጆሹአ ቺፕቴግን አስከትሎ መሆኑን የአለም አቀፍ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ አመልክቷል፡፡ ሪከርድ ለመስበር ለውድድሩ በቂ ዝግጅት አድርጌ ነበር ያለው አትሌት ዮሚፍ ቀጄልቻ ሪከርዱ ባይሳካም ባገኘሁት ውጤት ተደስቻለሁ ብሏል።
21ኛው ቅድሚያ ለሴቶች የ5 ኪ.ሜትር የሩጫ ውድድር በአዲስ አበባ ተካሄደ
Mar 17, 2024 137
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦21ኛው ቅድሚያ ለሴቶች የ5 ኪ.ሜ. የሩጫ ውድድር ዛሬ ማለዳ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ የሚያዘጋጀውና ሴቶች ብቻ የሚወዳደሩበት የ5 ኪ.ሜ የሩጫ ውድድር ዛሬ በአዲስ አበባ ተካሄዷል፡፡ የ2016 ሳፋሪኮም ቅድሚያ ለሴቶች የሚል መጠሪያ በተሰጠው የ5 ኪ.ሜ ሩጫ ውድድር 16 ሺህ ሴቶች ተሳትፈውበታል፡፡ "የሴቶችን አቅም እንደግፍ፤ ለውጥን እናፋጥን "በሚል መሪ ሃሳብ በተደረገው ውድድር የተካፈሉ ተሳታፊዎች ቁጥር በውድድሩ ታሪክ ከፍተኛው መሆኑ ተገልጿል፡፡ በውድድሩ ላይ ከአገር ውስጥ በተጨማሪ ከተለያዩ አገሮች የመጡ ከአርባ በላይ ሴቶች መሳተፋቸው ታውቋል፡፡ ኢትዮጵያና አየርላንድ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የጀመሩበትን 30ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ 35 አየርላንዳውያን በውድድሩ ተሳትፈዋል፡፡ ታላቁ ሩጫ የ21ኛ ዓመት ምሥረታ በዓሉን አስመልክቶ ከሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ሚኒስትሯ ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያና አጋሮቹ በሴቶች ዙሪያ ለሚከናወኑ ተግባራት እያደረጉት ላለው ድጋፍ ምስጋና ማቅረባቸው ይታወሳል። የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ ወ/ሮ ዳግማዊት አማረ ተቋሙ ባለፉት 21 ዓመታት ሴቶችን ለማብቃትና በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ያሉ ሴቶችንና በጎ አድራጎት ተቋማትን ለመደገፍ መቻሉን በመግለጫው ላይ መናገራቸው ይታወሳል፡፡ በማስጀመሪያ መርኃ-ግብሩ ላይ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ፣ ሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴ የአዲስ አበባ ከተማ ባህልና ስፖርት ቢሮ ሃላፊ ዶክተር ሂሩት ካሰው፣ አትሌት መሰረት ደፋርና ሌሎች ታዋቂ ግለሰቦች ተገኝተዋል። በውድድር ጉታኒ ሻንቆ 1ኛ፣ ብርነሽ ደሴ 2ኛ ፣ መቅደስ ሽመልስ 3ኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቀዋል፡፡
ስፖርቱን ከመንግስት ድጎማ ጥገኝነት አላቆ ራሱን እንዲችል ለማድረግ ስራዎች እየተከናወኑ ነው - የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ
Mar 16, 2024 203
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የስፖርቱን ዘርፍ ከመንግስት ድጎማ ጥገኝነት አላቆ ራሱን እንዲችል ለማድረግ ለፌዴሬሽኖችና ማህበራት ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ የከተማዋ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ አስታወቀ። በመዲናዋ ከሚገኙ የስፖርት ፌዴሬሽኖችና ማህበራት ውስጥ 10ሩ ራሳቸውን ከድጎማ ማላቀቅ የሚያስችሉ የመመዘኛ መስፈርቶችን የማሟላት ሂደት በማጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ ቢሮው ገልጿል። ቢሮው ይህን ያለው የአዲስ አበባ ከተማ ስፖርት ምክር ቤት 14ኛው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ዛሬ በአዲስ አበባ ባካሄደበት ወቅት ነው። የቢሮው ኃላፊና የምክር ቤቱ ምክትል ሰብሳቢ በላይ ደጀን ባለፈው አንድ ዓመት በስፖርቱ ዘርፍ የተከናወኑ ስራዎችን አስመልክቶ ለጠቅላላ ጉባኤው ሪፖርት አቅርበዋል። በ2015 ዓ.ም የአዲስ አበባ ስፖርት ምክር ቤት ባደረገው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፥ ምክር ቤቱ ስፖርቱን ከበጀት ድጎማ ለማላቀቅ በትኩረት መስራት እንዳለበት አሳስበው ነበር። የወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊው በላይ ደጀን በተለይ ለኢዜአ እንደገለጹት ቢሮው በመዲናዋ የሚገኙ 36 የስፖርት ፌዴሬሽኖችና ማህበራት ከመንግስት በጀት እንዲላቀቁ እየሰራ ነው። በዚህም የተለያዩ ስፖርቶች ራሳቸውን ችለዋል የሚያስብላቸውን መመዘኛዎች እንዲያሟሉ ቢሮው ድጋፍና ክትትል እያደረገ መሆኑን አመልክተዋል። ብስክሌት፣ ውሃ ዋና፣ ወርልድ ቴኳንዶ፣ ኢንተርናሽናል ቴኳንዶና ጅምናስቲክ የስፖርት ማህበራትና ፌዴሬሽኖች መስፈርቶቹን ለማሟላት እየሰሩ ከሚገኙት መካከል ይጠቀሳሉ። በራስ አቅም በጀት መመደብ፣ የሰው ኃይል መቅጠር፣ አደረጃጀትና ሀብት ማሰባሰብ ላይ የሚሰራ የገበያ ቡድን ማወቀር ከመመዘኛዎቹ መካከል እንደሚገኙበት ነው ኃላፊው ያነሱት። አትሌቲክስና እግር ኳስ ፌዴሬሽኖች በራሳቸው አቅም ከመንቀሳቀስ አኳያ እንደ መልካም ተሞክሮ እንደሚነሱ አመልክተዋል። ሌሎችም የስፖርት ፌዴሬሽኖችና ማህበራት ከድጎማ በጀት እንዲላቀቁ የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ በ2016 በጀት ዓመት ለስፖርት ፌዴሬሽኖችና ማህበራት ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት መመደቡንና ይህም ከባለፈው በጀት ዓመት አንጻር የ4 ሚሊዮን ብር ገደማ ብልጫ እንዳለው አንስተዋል። ከስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ጋር በተገናኘም በመዲናዋ 1 ሺህ 236 የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎች አገልግሎት እየሰጡ ሲሆን 741ዱ ባለፉት አምስት ዓመታት የተገነቡ መሆናቸውን ነው ኃላፊው የገለጹት። በ2015 ዓ.ም 13 የመደመር ትውልድ የሕጻናት እና ወጣቶች የመጫወቻና የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎች መገንባታቸውን ጠቅሰው፥ በ2016 ዓ.ም በጀት ዓመት እስከ አሁን 38 የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች እንደተገነቡ ገልጸዋል። በሌላ በኩል በአዲስ አበባ በ11ዱም ክፍለ ከተሞች በ19 የስፖርት ዓይነት 123 የታዳጊ ፕሮጀክቶች መከፈታቸውንም ነው ያነሱት። ስፖርትን ባህሉ ያደረገ ማኅበረሰብ ለመፍጠር በመኖሪያ፣ በመማሪያና በስራ አካባቢ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ፕሮግራም ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የአካባቢ የጤና ቡድኖችን በማጠናከር ሕብረተሰቡ ጤናውን ከመጠበቅ ባሻገር የእርስ በእርስ ግንኙነቱን እንዲያዳብር እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በጠቅላላ ጉባኤው የአዲስ አበባ ከተማ ስፖርት ምክር ቤት ለኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉና የስፖርት አፍቃሪ ጌታ ዘሩ ለሀገር የስፖርት እድገት ላበረከቱት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የእውቅና ሽልማት አበርክቷል። ጠቅላላ ጉባኤው በስፖርት ማህበራት ስራ አስፈጻሚነት ከአራት ዓመት በላይ ለሰሩ 47 ሰዎች የእውቅና ሽልማት በመስጠት በክብር አሰናብቷል። በተጨማሪም ጉባኤው ለመዲናዋ ሁለንተናዊ የስፖርት ዕድገት አስተዋጽኦ እያበረከቱ ላሉ ክለቦች፣ ተቋማትና ማህበራት እውቅና ሰጥቷል።
የትምህርት ቤቶች ስፖርት ውድድሮች ተተኪ ስፖርተኞች ለማፍራት ሚናቸውን እንዲወጡ ድጋፍ ይደረጋል - ከንቲባ ከድር ጁሃር
Mar 16, 2024 127
ድሬደዋ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፡- የትምህርት ቤቶች ስፖርታዊ ውድድሮች የድሬዳዋን የስፖርት ትንሳኤ በማሳካት ምርጥና ተተኪ ስፖርተኞች ለማፍራት ሚናቸውን እንዲወጡ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚደረግ የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባና የስፖርት ምክርቤት ሰብሳቢ ከድር ጁሃር ተናገሩ። የዘንድሮ የድሬዳዋ ዓመታዊ የትምህርት ቤቶች የስፖርት ውድድር ዛሬ ተጀምሯል። ውድድሩን ያስጀመሩት የድሬደዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃርና የድሬደዋ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሱልጣን አልይ ናቸው። አቶ ከድር ጁሃር በወቅቱ እንደተናገሩት ፤ የትምህርት ቤቶች ስፖርታዊ ውድድሮች ተተኪና ምርጥ ስፖርተኞች መፍልቂያ ናቸው። እነዚህን የስፖርት ውድድሮች በመደገፍና በመከታተል ለከተማችን የስፖርት ዝናና ትንስኤ መሳካት መሠረታዊ ሚና እንዲጫወቱ ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል። ስፖርተኞች በታላቅ ስፖርታዊ ስነምግባር ጨዋታቸውን በማካሄድ ያላቸውን አንድነትና ፍቅር ማጠናከር እንዳለባቸው አሳስበዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ በበኩላቸው፤ በገጠርና በከተማ የሚገኙ ትምህርት ቤቶች በቂና ምቹ የስፖርት ማዞተሪያዎች እንዲኖራቸው እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። በየዓመቱ ከሚካሄዱ ውድድሮች በተጨማሪ የውስጥ ጨዋታዎች በመካሄድ ተተኪ ስፖርተኞችን በመመልመል ለድሬደዋ ስፖርት ከፍታ አስተዋጽኦ ማድረጋቸው ተናግረዋል ። ዛሬ በተጀመረው ዓመታዊ የትምህርት ቤቶች ስፖርታዊ ውድድሮች ላይ 18 የአንደኛ ደረጃ እና 22 የሁለተኛ ትምህርት ቤቶች ስፖርተኞች የሚሳተፉ ሲሆን ፤ በተለያዩ የስፖርት ዓይነቶች ውድድሩ ለ45 ቀናት እንደሚቀጠል ተገልጿል።
በትግራይ ክልል በእግር ኳስ ዘርፍ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የሚያስችል ስልጠና እየተሰጠ ነው
Mar 15, 2024 132
መቀሌ፤ መጋቢት 6/2016 (ኢዜአ) ተተኪና ታዳጊ የእግር ኳስ ስፖርተኞችን ለማፍራት የሚያስችል የስልጠና ፕሮጀክት በትኩረት እየተሰጠ መሆኑን በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ስፖርት ኮሚሽን የእግር ኳስ ፌዴሬሸን ፅህፈት ቤት አስታወቀ። የጽህፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ ሞጎስ ተፈራ ለኢዜአ እንደገለፁት፣ የተገኘውን ሰላም በመጠቀም በመቀሌ ከተማ በስምንት ማሰልጠኛ ማእከላት ከአምስት እስከ 20 ዓመት ዕድሜ ክልል ለሚገኙ ታዳጊ ህፃናትና ወጣቶች ስልጠናው እየተሰጠ ይገኛል። በግል ተነሳሽነት አቅምና ፍላጎቱ ባላቸው ወጣት አሰልጣኞች እየተሰጡ የሚገኙ የእግር ኳስ ስፖርት ስልጠናዎችም ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልፀዋል። በያዝነው ዓመት ከየካቲት ወር ጀምሮ እየተሰጠ ያለው ሳይንሳዊ የእግር ኳስ ፕሮጀክት ስልጠና የሚሰጠው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የአሰልጣኞች ስልጠና በወሰዱ 80 የእግር ኳስ ባለሙያዎች መሆኑንም ኃላፊው ተናግረዋል። ክልላቸውን ብሎም አገራቸውን የሚወክሉ ከ5 ሺህ በላይ ሰልጣኞች ተመልምለው ስልጠናውን በመከታተል ላይ መሆናቸውንም ኃላፊው ጠቁመዋል። በአገር ውስጥና በውጭ የሚገኙ የስፖርት አፍቃሪዎች እና ደጋፊዎች ስልጠናውን በገንዘብ፣ በስፖርት ትጥቅና ኳሶችን በማቅረብ ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ አቶ ሞጎስ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል። ስልጠና እየወሰዱ የሚገኙት ታዳጊና ወጣት ስፖርተኞች በየዕድሜ እርከናቸው በሲ እና በቢ ቡድን ተደልድለው በእግር ኳስ ውድድር እንዲሳተፉ እየተደረገ መሆኑንም ገልጸዋል። የእግር ኳስ ፕሮጀክት ስልጠናው መሰጠት ከተጀመረ አምስት ወራት እንዳለፈው የገለፀው በሃውልቲ ክፍለ ከተማ ታዳጊና ወጣቶችን በማሰልጠን ላይ የሚገኘው አሰልጣኝ ሚካኤሌ አመሃ ስልጠናው ጤናማና በስነ ልቦና ብቁ የሆነ ስፖርተኛ ለማፍራት ትልቅ ዋጋ እንዳለው ተናግሯል። በተጨማሪም የፕሮጀክት ስልጠናው ከክልሉ ባሻገር በአገራችን በሚገኙ የእግር ኳስ ክለቦች ውስጥ ገብተው ለመወዳደር ብሎም የኢትዮጵያን ስም የሚያስጠሩ ፕሮፌሽናል ስፖርተኞችን ለማፍራት እንደሚያስችል ገልጿል። በአሰልጣኞቻቸውና በቤተሰቦቻቸው እየተደረገላቸው የሚገኘው የስልጠናና የትጥቅ ድጋፍ አቅም ፈጥሮላቸው በተለያዩ ክለቦች ገብተው እንዲወዳደሩ ከማገዝ ባለፈ አገራቸውን በመወከል ስሟን ለማስጠራት ጠቀሜታው ከፍተኛ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ስልጠናውን እየተከታተሉ የሚገኙት ወጣት ቃልአብ ኪዳኑና ወጣት ዮናስ ጌድዮን ናቸው።
በፕሪሚየር ሊጉ ቀዳሚ ስፍራ ላይ የሚገኙት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክና መቻል የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Mar 15, 2024 130
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2016(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት መርሐ ግብር የሁለተኛ ቀን ውሎ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመቻል የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ በድሬዳዋ ስታዲየም ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ ይካሄዳል። በአሰልጣኝ በጸሎት ልዑልሰገድ እየተመራ በፕሪሚየር ሊጉ ጠንካራ ግስጋሴ እያደረገ የሚገኘው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በውድድር ዓመቱ እስከ አሁን ባደረጋቸው 17 ጨዋታዎች በ11ዱ ሲያሸንፍ በ3ቱ ተሸንፏል፤ ሶስት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ 31 ግቦችንም ሲያስቆጥር 16 ጎሎች አስተናግዷል፤ በ36 ነጥብ እና በ15 የግብ ክፍያ ሊጉን እየመራ ይገኛል። ንግድ ባንክ ባለፉት አምስት ተከታታይ የሊጉ ጨዋታዎች በሁለቱ ሲያሸንፍ በሁለቱ ሸንፈት አጋጥሞታል፤ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው መቻል በፕሪሚየር ሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው 17 ጨዋታዎች 10ሩን ሲያሸንፍ 4 ጊዜ ተሸንፏል። ሶስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 23 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 18 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ክለቡ በ33 ነጥብና በ5 የግብ ክፍያ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የመቻል አሰልጣኝ ገብረክርስቶስ ቢራራ ክለቡ በ17ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከባህር ዳር ከተማ ጋር በነበረው ጨዋታ በተጋጣሚ ቡድን አሰልጣኝ ላይ ለጠብ የሚያነሳሳ የስነ-ምግባር ድርጊት ፈጽመዋል በሚል ለአራት ጨዋታ መታገዳቸውን ተከትሎ ቡድናቸውን በሜዳ ተገኝተው አይመሩም። በተጨማሪም አሰልጣኙ አምስት ሺህ ብር እንዲከፍሉ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር አመራርና ስነ-ስርዓት ኮሚቴ መወሰኑ ይታወቃል። በሌላኛው የ18ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከቀኑ 10 ሰዓት ድሬዳዋ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በአሰልጣኝ ኮማንደር ሽመልስ አበበ የሚመራው ድሬዳዋ ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሶስቱ ሲያሸንፍ በሁለቱ አቻ ወጥቷል። ክለቡ በ25 ነጥብ 8ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ሀዋሳ ከተማ በበኩሉ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ጨዋታዎች በሶስቱ ሲያሸንፍ በአንዱ ሽንፈት አጋጥሞታል። አንድ ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። በአሰልጣኝ ዘርዓይ ሙሉ የሚመራው ሀዋሳ ከተማ በ22 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በተያያዘ ዜና ትናንት በተደረጉ የ18ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ባህር ዳር ከተማ ኢትዮጵያ ቡናን 3 ለ 1፤ አዳማ ከተማ ሀምበሪቾ ዱራሜን 3 ለ 0 አሸንፈዋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬ ይጀመራሉ
Mar 14, 2024 144
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2016 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 18ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ በሚደረጉ ሁለት ጨዋታዎች ይጀመራል። በድሬዳዋ ስታዲየም በሚካሄደው ጨዋታ ባህር ዳር ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና ከቀኑ 10 ሰዓት ይገናኛሉ። ባህር ዳር ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሁለቱ ሲያሸንፍ በሁለት ጨዋታ ተሸንፎ አንድ ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። በደረጃ ሰንጠረዡም በ26 ነጥብ 6ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል፤ አንድ ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። ኢትዮጵያ ቡና በ29 ነጥብ 4ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በሌላኛው 18ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታ ሀምበሪቾ ዱራሜ ከአዳማ ከተማ ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። በፕሪሚየር ሊጉ የመጀመሪያ ተሳትፎውን እያደረገ የሚገኘው ሀምበሪቾ ዱራሜ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በአራቱ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ክለቡ በ7 ነጥብ የመጨረሻውን 16ኛ ደረጃ ይዞ ይገኛል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በአንዱ ሲሸነፍ በሶስቱ አቻ ወጥቷል፤ በ24 ነጥብም 8ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የፕሪሚየር ሊጉ የ18ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ነገም ቀጥሎ ሲውል ድሬዳዋ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት፤ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በደረጃ ሰንጠረዡ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ከሚገኘው መቻል ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የ18ኛ ሳምንት ጨዋታዎች እስከ መጋቢት 8 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሊጉን በ36 ነጥብ እየመራ ይገኛል።
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ከመማር ማስተማር ጎን ለጎን ለስፖርት ዘርፍ ትኩረት ሰጥቷል - ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር)
Mar 8, 2024 294
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 29/2016 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ከመማር ማስተማር ጎን ለጎን ለስፖርት ዘርፍ ትኩረት ሰጥቷል ሲሉ የዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) ገለጹ። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዓመታዊ የስፖርት ፌስቲቫል ዛሬ ተጀምሯል። በማስጀመሪያ መርኃ ግብሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዘዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር)ን ጨምሮ ዩኒቨርስቲው ማኅበረሰብ አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የስፖርት ፌስቲቫሉ "ስፖርት ለሠላምና ለአብሮነት" በሚል መሪ ኃሳብ የሚካሄድ ሲሆን በዩኒቨርሲቲው ሥር የሚገኙ ኮሌጆች በውድድሩ ላይ ይሳተፋሉ። እግር ኳስ፣ አትሌቲክስ፣ ቅርጫት ኳስ፣ ቮሊቦልና ፓራ ኦሊምፒክ ፌስቲቫሉ የሚካሄድባቸው የስፖርት አይነቶች ናቸው ተብሏል። በፌስቲቫሉ ላይ ከ2 ሺህ በላይ ተማሪዎች እንደሚሳተፉ ተገልጿል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዘዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ ተማሪዎች ከመደበኛ ትምህርታቸው በተጨማሪ አዕምሯቸውንና አካላቸውን የሚያጎለብቱበት የስፖርት አማራጭ ሊመቻችላቸው ይገባል። ስፖርት ከአዕምሯዊና አካላዊ ማጎልበት ጠቀሜታ ባሻገር እርስ በእርስ ልምድ መለዋወጫ መድረክ መሆኑን ጠቅሰው የ2016 የዩኒቨርሲቲው የስፖርት ፌስቲቫልም ይህንን ታሳቢ በማድረግ የተዘጋጀ መሆኑን ነው የተናገሩት። የስፖርት ፌስቲቫሉ በተጠናከረ ሁኔታ ቀጣይነት እንዲኖረው ለማስቻል የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎችን ማደስ፣ ደረጃ ማሻሻልና አዳዲስ ግንባታ ማከናወን ላይ በትኩረት እንደሚሰራ ዩኒቨርስቲው አመልክቷል። ፌስቲቫሉ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የተያዘውን አገራዊ እቅድ በማሳካት ረገድ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተጠቁሟል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዓመታዊ የስፖርት ፌስቲቫል እስከ መጋቢት 14 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል።
የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ዓመታዊ የስፖርት ፌስቲቫል ተጀመረ
Mar 8, 2024 280
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2016(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያዘጋጀው ዓመታዊ የስፖርት ፌስቲቫል ዛሬ ተጀምሯል። በስፖርት ፌስቲቫሉ መክፈቻ ሥነ-ሥርዓት ላይ ተማሪዎች፣የዩኒቨርስቲው ማኅበረሰብ አባላትና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። ፌስቲቫሉ "ስፖርት ለሰላምና ለአብሮነት" በሚል መሪ ኃሳብ የሚካሄድ ሲሆን በዩኒቨርሲቲው ሥር የሚገኙ ኮሌጆች በውድድሩ ላይ ይሳተፋሉ። እግር ኳስ፣ አትሌቲክስ፣ ቅርጫት ኳስ፣ ቮሊቦልና ፓራ ኦሊምፒክ ፌስቲቫሉ የሚካሄድባቸው የስፖርት አይነቶች ናቸው ተብሏል። በፌስቲቫሉ ላይ ከ2 ሺህ በላይ ተማሪዎች እንደሚሳተፉ ተገልጿል። የስፖርት ፌስቲቫሉ በተጠናከረ ሁኔታ ቀጣይነት እንዲኖረው ለማስቻል የስፖርት ማዘውተሪያ ቦታዎችን ማደስ፣ ደረጃ ማሻሻልና አዳዲስ ግንባታ ማከናወን ላይ በትኩረት እንደሚሰራ ዩኒቨርስቲው አመልክቷል። ፌስቲቫሉ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የተያዘውን ሀገራዊ እቅድ በማሳካት ረገድ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተጠቁሟል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ዓመታዊ የስፖርት ፌስቲቫል እስከ መጋቢት 14 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል።
13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች ዛሬ ይጀመራል
Mar 8, 2024 284
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2016(ኢዜአ)፦13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች ዛሬ በጋና ይጀመራል። ውድድሩን ያዘጋጁት የአፍሪካ ኅብረት ከአፍሪካ ኦሊምፒክ ኮሚቴዎች ማኅበርና ከአፍሪካ ስፖርት ኮንፌዴሬሽኖች ማኅበር ጋር በመተባበር ነው። በውድድሩ ላይ ከ4000 በላይ አትሌቶች በ29 የስፖርት አይነቶች የሚሳተፉ ሲሆን ከስፖርት አይነቶቹ ስምንቱ በፓሪስ በሚደረገው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ለማለፍ የሚያስችሉ ውድድሮች ናቸው። ኢትዮጵያም በውድድሩ በዘጠኝ ስፖርቶች 149 ስፖርተኞች የምታሳትፍ ሲሆን ከነዚህም አምስቱ የኦሊምፒክ ውድድሮችና አራቱ የኦሊምፒክ ውድድር ያልሆኑ ስፖርቶች ናቸው። አትሌቲክስ፣ እግር ኳስ፣ ውሃ ዋና፣ ቴኒስ፣ ጠረጴዛ ቴኒስ፣ ቦክስ፣ ቅርጫት ኳስ፣ ብስክሌትና ወርልድ ቴኳንዶ ኢትዮጵያ የምትሳተፍባቸው የውድድር አይነቶች ናቸው። ዝላይና ዲስከስ ውርወራ ኢትዮጵያ በአትሌቲክሱ ዘርፍ ከምትሳተፍባቸው የውድድር አይነቶች መካከል ይጠቀሳሉ። በአፍሪካ ጨዋታዎች ላይ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን በተለያዩ ዙሮች ተከፋፍሎ ጋና መግባቱን ኢዜአ ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ያገኘው መረጃ ያመለክታል። 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች የመክፈቻ ሥነ-ሥርዓት አክራ በሚገኘው የጋና ዩኒቨርሲቲ ስፖርት ስታዲየም ይከናወናል። በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳ ፋኪ ማህማት፣ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን የጤና፣ የሰብዓዊ ጉዳዮችና ማኅበራዊ ልማት ኮሚሽነር አምባሳደር ሚናታ ሳማቴ ሴሱማና ሌሎች የኮሚሽኑ አመራሮች እንደሚገኙ ከአፍሪካ ሕብረት የተገኘው መረጃ ያሳያል። ውድድሩ በአክራ፣ ኩማሲና ኬፕ ኮስት ከተሞች የሚካሄድ ሲሆን 13ኛው የአፍሪካ ጨዋታዎች እስከ መጋቢት 14 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል። ውድድሩ እ.አ.አ በ2023 መካሄድ የነበረበት ቢሆንም በውድድሩ አዘጋጆች መካከል በነበረ የገበያ መብቶች አለመግባባት ወደ 2024 መዘዋወሩ የሚታወስ ነው። የአፍሪካ ጨዋታዎች (በቀድሞ ስያሜው የመላው አፍሪካ ጨዋታዎች) በየአራት ዓመቱ የሚካሄድ ውድድር ነው። የአህጉራዊው ስፖርት ውድድር ኃሳብ የተጠነሰሰው እ.አ.አ በ1963 በሴኔጋል በተካሄደ የስፖርት ፌስቲቫል ነው። በዛው ዓመት የአፍሪካ የወጣትና ስፖርት ሚኒስትሮች ሴኔጋል ላይ ባደረጉት ስብስባ ውድድሩ የመላው የአፍሪካ ጨዋታዎች ተብሎ እንዲካሄድ ከውሳኔ ላይ ደረሱ። የመጀመሪያው ውድድር እ.አ.አ በ1965 በኮንጎ ብራዛቪል የተካሄደ ሲሆን በውድድሩ ላይ ከ30 አገራት የተወጣጡ ከ2500 በላይ ስፖርተኞች ተሳትፈዋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 17ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጀመራል
Mar 7, 2024 285
አዲስ አበባ፤የካቲት 28/216 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 17ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬ መካሄድ ይጀምራሉ።በዛሬው መርሐ ግብር ሀዋሳ ከተማ ከሻሸመኔ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት እንዲሁም መቻል ከባህር ዳር ከተማ ከምሽቱ 1 ሰዓት በድሬዳዋ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሀዋሳ ከተማ በፕሪሚየር ሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች በሁለቱ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። አንድ ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። ክለቡ በ19 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው ሻሸመኔ ከተማ በበኩሉ ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በሁለቱ ሲሸነፍ በሁለቱ ነጥብ ተጋርቷል። ሻሸመኔ ከተማ በ12 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በሌላኛው የ17ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መቻል ከባህር ዳር ከተማ ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። መቻል ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች በሁለቱ ድል ሲቀናው በሁለቱ ሽንፈት አስተናግዷል። አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በ33 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በአንጻሩ ባህር ዳር ከተማ ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንዱን ብቻ ነው። በሶስቱ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። ባህር ዳር በ23 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። የ17ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ነገም ሲቀጥሉ አዳማ ከተማ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 10 ሰዓት፤ ሲዳማ ቡና ከ ወልቂጤ ከተማ ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። የፕሪሚየር ሊጉ የ17ኛ ሳምንት መርሐ ግብር እስከ መጋቢት 1 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሪሚየር ሊጉን በ35 ነጥብ እየመራ ይገኛል።
የቡድን ሥራ የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ አድርጓል- አትሌቶችና የቡድን መሪዎች
Mar 6, 2024 175
አዲስ አበባ፤ የካቲት 27/2016(ኢዜአ)፦በ19ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና እና በስድስተኛው የአፍሪካ አገር አቋራጭ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የነበረው የቡድን ሥራ የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ ማድረጉን አትሌቶችና የቡድን መሪዎች ገለጹ። በ19ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና እና በስድስተኛው የአፍሪካ አገር አቋራጭ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ለተሳተፉ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልዑካን ቡድኖች ትናንት የእውቅና መርሃ-ግብር ተካሂዷል። በስኮትላንድ በተካሄደው ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በሁለት የወርቅ፣ በአንድ የብርና በአንድ የነሐስ በድምሩ አራት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ከዓለም አምስተኛ ከአፍሪካ አንደኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በቱኒዚያ በተካሄደው ስድስተኛው የአፍሪካ አገር አቋራጭ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ በሁለት የወርቅ፣ አምስት የብር እና ሦስት የነሐስ በድምሩ አሥር ሜዳሊያዎች በመያዝ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቋ ይታወቃል። በዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና በ800 ሜትር ሴቶች የወርቅ ሜዳሊያ ያገኘችው አትሌት ፅጌ ድጉማ ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ታሪክ በርቀቱ የመጀመሪያ የወርቅ ሜዳሊያ ማስገኘቷ ደስታን እንደፈጠረባት ገልጻለች። ለሻምፒዮናው ጥሩ ዝግጅት ማድረጓንና በግሏ የነበራት የራስ መተመማን ውድድሩን እንድታሸንፍ እንዳደረጋት ተናግራለች። በፈረንሳይ ፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በመሳተፍ ውጤት ለማስመዝገብ እንደምትፈልግ ነው የገለፀችው። በሻምፒዮናው በ1 ሺህ 500 ሜትር የወርቅ ሜዳሊያ ያገኘችው አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ፤ በውድድሩ ላይ የነበረው የቡድን ሥራ ውጤቱ እንዲገኝ አድርጓል ብላለች። የስድስተኛው የአፍሪካ አገር አቋራጭ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን መሪ ናስር ሁሴን በበኩሉ፤ በውድድሩ ፈታኝ ሁኔታዎች የነበሩ ቢሆንም አትሌቶቹ ጫናውን በመቋቋም መልካም ውጤት ማስመዝገባቸውን ገልጿል። በተለይም በተስፈኛ አትሌቶች የተገኘው ውጤት በተተኪ አትሌቶች ላይ በይበልጥ ከተሰራ ውጤት ማግኘት እንደሚቻል ተናግሯል። የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ አትሌቶች በዓለም መድረኮች የአገራቸውን ስምና ሰንደቅ ዓላማ ከፍ አድርገው የሚያስጠሩ ናቸው። በቱኒዚያና ስኮትላንድ የተመዘገቡት ውጤቶች አትሌቶች በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ ሆነው አገር የሰጠቻቸውን አደራ መወጣት እንደሚችሉ ያሳዩ ናቸው ብለዋል። ሚኒስትር ዴኤታው የኢትዮጵያ አትሌቶች የአሸናፊነትና የፅናት ተምሳሌት እንደሆኑም ነው የተናገሩት። በቀጣይ በፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ከተፎካካሪዎች በልጦ ለመገኘትና የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ጠንካራ ዝግጅት ማድረግ እንደሚገባም ገልፀዋል። መንግሥት ኢትዮጵያ በቀጣይ በምትሳተፍባቸው ዓለም አቀፍና አህጉራዊ ስፖርታዊ መድረኮች የተሻለ ውጤት እንድታገኝ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ፤ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በውድድሮቹ አመርቂ ውጤት በማስመዝገባችሁ ኢትዮጵያ ኮርታባችኋለች ብለዋል። ውጤቶቹ አበረታች ቢሆኑም በፓሪስ የኦሊምፒክ ጨዋታዎችና በቀጣይ በሚከናወኑ ውድድሮች የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ብዙ መሥራት እንደሚገባ አመላካች መሆኑን ገልፀዋል። በኦሊምፒክ ጨዋታዎች በአትሌቲክስ ስፖርት ለመሳተፍ የሚያስችሉ ዝግጅቶች መጀመራቸውን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ ዳዊት አስፋው፤ በውድድሮቹ ላይ የተገኙት ወጤቶች በፈረንሳይ ፓሪስ ለሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታ ስንቅ የሚሆን ነው ብለዋል። ኦሊምፒክ ኮሚቴው ለአትሌቲክሱ ስፖርት እድገት ድጋፉን ማድረግ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አትሌትክስ ፌዴሬሽን ለልዑካን ቡድኑ አባላት በአጠቃላይ ከ800 ሺህ ብር በላይ ሽልማት አበርክቷል።
የኢትዮጵያ አትሌቶች የአሸናፊነትና የፅናት ተምሳሌት ናቸው-አምባሳደር መስፍን ቸርነት
Mar 5, 2024 181
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2016(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አትሌቶች የአሸናፊነትና የፅናት ተምሳሌት መሆናቸውን የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት ገለጹ። በፈረንሳይ ፓሪስ ለሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በአትሌቲክሱ የተሻለ ውጤት ለማምጣት ከወዲሁ ጠንካራ ዝግጅት ማድረግ እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል። በ19ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና እና በስድስተኛው የአፍሪካ አገር አቋራጭ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ለተሳተፉ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልዑካን ቡድኖች የእውቅና መርሐ ግብር ተካሄዷል። በመርሐ ግብሩ ላይ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉና ሌሎች የፌዴሬሽኑ አመራሮች እንዲሁም ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። አምባሳደር መስፍን ቸርነት በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ የኢትዮጵያ አትሌቶች በዓለም መድረኮች የአገራቸውን ስምና ሰንደቅ ዓላማ ከፍ አድርገው የሚያስጠሩ ናቸው። በቱኒዚያና ስኮትላንድ የተመዘገቡት ውጤቶች አትሌቶች በየትኛውም ሁኔታ ውስጥ ሆነው አገር የሰጠቻቸውን አደራ መወጣት እንደሚችሉ ያሳዩ ናቸው ብለዋል። ሚኒስትር ዴኤታው የኢትዮጵያ አትሌቶች የአሸናፊነትና የፅናት ተምሳሌት እንደሆኑም ነው የተናገሩት። በቀጣይ በፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ከተፎካካሪዎች በልጦ ለመገኘትና የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ጠንካራ ዝግጅት ማድረግ እንደሚገባም ገልጸዋል። መንግስት ኢትዮጵያ በቀጣይ በምትሳተፍባቸው ዓለም አቀፍና አህጉራዊ ስፖርታዊ መድረኮች የተሻለ ውጤት እንድታገኝ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በውድድሮቹ አመርቂ ውጤት በማስመዝገባችሁ ኢትዮጵያ ኮርታባችኋለች ብለዋል። ውጤቶቹ አበረታች ቢሆኑም በፓሪስ የኦሊምፒክ ጨዋታዎችና በቀጣይ በሚከናወኑ ውድድሮች የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ብዙ መስራት እንደሚገባ አመላካች መሆኑን ገልጸዋል። በኦሊምፒክ ጨዋታዎች በአትሌቲክስ ስፖርት ለመሳተፍ የሚያስችሉ ዝግጅቶች መጀመራቸውን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ አቶ ዳዊት አስፋው በውድድሮቹ ላይ የተገኙት ወጤቶች በፈረንሳይ ፓሪስ ለሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታ ስንቅ የሚሆን ነው ብለዋል። ኦሊምፒክ ኮሚቴው ለአትሌቲክሱ ስፖርት እድገት ድጋፉን ማድረግ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አትሌትክስ ፌዴሬሽን ለልዑካን ቡድኑ አባላት በአጠቃላይ ከ800 ሺህ ብር በላይ ሽልማት አበርክቷል።
በዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና የላቀ ውጤት ያስመዘገበው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልዑካን ቡድን አዲስ አበባ ገባ
Mar 5, 2024 232
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 26/2016 (ኢዜአ)፦በስኮትላንድ ግላስኮው በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና የላቀ ውጤት ያስመዘገበው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልዑካን ቡድን አዲስ አበባ ገባ። ልዑካን ቡድኑ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ሲደርስ የባህልና የስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ፣ የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ዋና ፀሐፊ ዳዊት አስፋው፣ የፌዴሬሽኑ አመራሮችና ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ሻምፒዮናው ከየካቲት 22 እስከ 24 ቀን 2016 ዓ.ም በስኮትላንድ ግላስኮው መካሄዱ ይታወቃል። በውድድሩ በ13 አትሌቶች የተወከለችው ኢትዮጵያ በሁለት የወርቅ፣ በአንድ የብርና በአንድ የነሐስ በድምሩ 4 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ከዓለም አምስተኛ ከአፍሪካ አንደኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ኢትዮጵያ በ800 ሜትር ሴቶች በፅጌ ዱጉማ እና በ1500 ሜትር በፍሬወይኒ ኃይሉ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። በ3000 ሜትር ሴቶች አትሌት ጉዳፍ ፀጋይ የብር እንዲሁም በ3000 ሜትር ወንዶች ሰለሞን ባረጋ የነሐስ ሜዳሊያ አግኝተዋል። ለአትሌቲክስ ልዑካን ቡድኑ በቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ አቀባበል ከተደረገ በኋላ የእውቅና መርሐ ግብር እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
በሶማሌ ክልል በከተማ አስተዳደሮች እና በዩኒቨርስቲ ክለቦች መካከል ሲካሄድ የቆየው የእግርኳስ ውድድር ትናንት ምሽት ተጠናቀቀ
Mar 4, 2024 189
ጅግጅጋ ፤ የካቲት 25/2016(ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል በስድስት ከተማ አስተዳደሮች እና በሁለት ዩኒቨርሲቲ ክለቦች መካከል በጅግጅጋ ስታድየም ሲካሄድ የቆየው የእግርኳስ ውድድር ትናንት ምሽት ተጠናቀቀ። ለሶስት ሳምንታት ሲካሄድ በቆየው ውድድር የተሳተፉት የጅግጅጋ፣ ጎዴ፣ ቀብሪደሃር፣ ቶግ ውጫሌ፣ ቀብሪበያህ፣ ደገሀቡር ከተማ አስተዳደሮች እና የጅግጅጋና ቀብሪደሃር ዩኒቨርሲቲዎች የእግር ኳስ ቡድኖች ናቸው። ትናንት በተካሄው የፍፃሚ ጨዋታ ጅግጅጋ ከተማ አስተዳደር የቀብሪ ደሃር ዩኒቨርሲቲን በማሸነፍ የዋንጫ ባለቤት ሆኗል። በፍጻሜ ጨዋታው ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ዶክተር ሁሴን ሃሺ፣ የብልፅግና ፓርቲ የሶማሌ ክልል ቅርንጫፍ ኃላፊ ኢንጂነር መሀመድ ሻሌ፣ የጅግጅጋ ከተማ ከንቲባ ኢንጂነር ሻፊ አህመድን ጨምሮ የጅግጅጋ ከተማ እግር ኳስ አፍቃሪያን ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ በአለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ከአፍሪካ አንደኛ ከዓለም አምስተኛ በመሆን አጠናቀቀች
Mar 4, 2024 257
አዲስ አበባ፤ የካቲት 25/2016 (ኢዜአ)፡- በ19ኛው የአለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ ከአፍሪካ አንደኛ ከዓለም አምስተኛ በመሆን አጠናቃለች። በስኮትላንድ ግላስጎ ሲካሄድ የነበረው 19ኛው የዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ትናንት ሌሊት ተጠናቋል። በውድድሩ ከተለያዩ ሀገራት የተውጣጡ ከ650 በላይ አትሌቶች የተሳተፉ ሲሆን ኢትዮጵያም በ800 ሜትር፣ በ1500 ሜትር እና በ3000 ሜትር ርቀቶች በ8 ሴቶች እና በ5 ወንዶች በድምሩ በ13 አትሌቶች ተሳትፋለች ፡፡ በሻምፒዮናው ኢትዮጵያ በሴቶች 800 ሜትር ፅጌ ዱጉማ እና በሴቶች 1500 ሜትር ፍሬወይኒ ሀይሉ የወርቅ ሜዳሊያን አሸንፈዋል። በሴቶች 3000 ሜትር ጉዳፍ ፀጋዬ የብር እንዲሁም በወንዶች 3000 ሜትር ሰለሞን ባረጋ የነሃስ ሜዳሊያ ለኢትዮጵያ ያስገኙ አትሌቶች መሆናቸውን ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የተገኘው መረጃ ያመላክታል። በዚህ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ ሁለት ወርቅ አንድ ነሀስ በአንድ ብር በአጠቃላይ በአራት ሜዳሊያዎችን በማግኘት በሜዳልያ ሰንጠረዥ ከአፍሪካ አንደኛ ከአለም አምስተኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቃለች።
የድሬዳዋ የከፍተኛ ዲቪዚዮን የክለቦች ውድድር ተተኪ ተጫዋቾች የተገኙበት ነው
Mar 3, 2024 167
ድሬደዋ፤ የካቲት 24 /2016( ኢዜአ)፡- የድሬደዋ የከፍተኛ ዲቪዚዮን የክለቦች ውድድር ተተኪና የቀድሞ ዝና ለመመለስ የሚያስችሉ ተጫዋቾች የተገኙበት መድረክ መሆኑ ተገለጸ። በድሬዳዋ አስተዳደር በ14 የከፍተኛ ዲቪዚዮን ክለቦች መካከል ሲካሄድ የሰነበተው ዓመታዊ የእግርኳስ ጨዋታ በመስቀለኛ ክለብ አሸናፊነት ተጠናቋል። በውድድሩ ማብቂያ ላይ የተገኙት የድሬደዋ አስተዳደር ከንቲባና የስፖርት ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ከድር ጁሃር በወቅቱ ለኢዜአ እንደተናገሩት ፤ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር ተጨማሪ ክለብ ለመፍጠር ለሚደረገው ጥረት ውድድሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል ። በተለይ ድሬዳዋ በኢትዮጵያ ደረጃ በእግር ኳስ የነበራትን ገናና ዝናና ስም ለመመለስ የሚያስችሉ ምርጥ ተጫዋቾች ያሏት መሆኑን በውድድሩ ተመልክተናል ብለዋል። እነዚህን ጅምር ስራዎች ይበልጥ ለማሳደግ በአዳጊ ወጣቶች ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ ይሰራል ብለዋል። የስፖርት ማዘውተሪያና መሠረተ ልማት በስፋት እየተከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል። የውድድሩ ሻምፒዮና የሆነው የመስቀለኛ ክለብ ዋና አሰልጣኝና የውድድሩ ኮኮብ አሰልጣኝ ተብላ የተመረጠችው የ27 ዓመቷ ወጣት ምስጋና አበባየሁ ለኢዜአ እንደተናገረችው ፤በተናበበ ትጋትና ቁርጠኝነት የተገኘው ድል አስደሳች ነው። ይህ ጅምር ውጤት በማስቀጠል በቀጣይ በድሬዳዋ ሆነ በአገር የእግርኳስ ሂደት ውስጥ ሴቶች ደማቅ አሻራ እንዲኖራቸው በአርአያነት እንደምትሰራ ገልፃለች ። " ምኞቴ ትላልቅ የአገራችንን ክለቦች አሰልጥኜ በአፍሪካ ውድድሮች ላይ ክስተት መሆን ነው የምፈልገው፤ ይሄን ደግሞ አደርገዋለሁ " ብላለች። እንደ ወጣቷ አሰልጣኝ ገለጻ፤ ወጣቶቹ የተሻለ ደረጃ እንዲደርሱ ላሉባቸው የትጥቅና የላብ መተኪያ ችግሮች የሚመለከታቸው አካላትና ስፖርት ወዳጁ የድሬዳዋ ባለሃብቶችና ህብረተሰብ ድጋፍ ማድረግ አለባቸው። በእውነት በተሰጠኝ ማዕረግ ተደስቻለሁ ፤ ችሎታዬን አሳድጌ ለድሬዳዋና ለብሔራዊ ቡድን የመጫወት ፍላጎቴን አሳካለሁ ያለው ደግሞ የውድድሩ ኮኮብ ተጫዋች ስንታየሁ አበባየሁ ነው። ከሶስት ወራት በፊት የተጀመረውና በ14 የድሬደዋ የከፍተኛ ዲቪዚዮን ክለቦች መካከል ሲካሄድ የሰነበተው ዓመታዊ ውድድር አሸናፊ የሆነው የመስቀለኛ ክለብ የወርቅ ሜዳሊያ ፣ የዋንጫና የ200ሺህ ብር ተሸላሚ ሆኗል። ሁለተኛ የወጣው ገንደ አብዲ ቦሩ የብር ሜዳሊያና የ150 ሺህ ብር ተሻላሚ ሲሆን ፤የነሐስ ሜዳሊያ ተሸላሚው የድሬ ካባ ደግሞ የ100 ሺህ ተበርክቶለታል ። የውድድሩ ኮኮብ አሰልጣኝ፣ግብ ጠባቂ ፣ተጫዋችና ግብ አስቆጣሪ የዋንጫና የዘመናዊ የስልክ ሞባይል ተሸላሚ ሆነዋል። የተዘጋጁትን ሽልማቶች የድሬዳዋ ከንቲባ ከድር ጁሃርና የካቢኔ አባላት እንዲሁም የአስተዳደሩ ስፖርትና ወጣቶች ኮሚሽን ከፍተኛ የአመራር አባላት አበርክተዋል።
የድሬዳዋ የከፍተኛ ዲቪዚዮን ክለቦች አመታዊ የሻምፒዮና የእግር ኳስ ጨዋታ ተጠናቀቀ
Mar 1, 2024 221
ድሬዳዋ ፤ የካቲት 22/2016(ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ አስተዳደር በ14 የከፍተኛ ዲቪዚዮን ክለቦች መካከል ሲካሄድ የሰነበተው አመታዊ የሻንፒዮና የእግርኳስ ጨዋታ ዛሬ ተጠናቀቀ ። ከህዳር 16 ቀን 2016 ጀምሮ ከሶስት ወራት በላይ የተካሄደው የሻምፒዮና የእግር ኳስ ጨዋታ በመስቀለኛ ክለብ አሸናፊነት ተጠናቋል። ዛሬ በተካሄደው የፍጻሜ ጨዋታ መስቀለኛ 06 ህብረትን (ደቻቱን) አራት ለባዶ በማሸነፍ የዋንጫ ባለቤት ሆኗል። በፍጻሜው የጨዋታ ስነ ስርአት ላይ የድሬደዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር፣ የካቢኔ አባላት፣ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ክለቦች አሰልጣኞችና ተጫዋቾችና የስፖርት ቤተሰቦች ታድመዋል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሁለት የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከሎች ይገነባሉ - የክልሉ ስፖርት ከሚሽን
Mar 1, 2024 235
አሶሳ፤ የካቲት 22/2016(ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በ361 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ሁለት ዘመናዊ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከሎች እንደሚገነቡ የክልሉ ስፖርት ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ የክልሉ ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ የሱፍ አልበሽር ለኢዜአ በሰጡት መግለጫ በክልሉ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል፡፡ ይህን ለማሳካትም በአሶሳ ዞን ኡራ ወረዳ የባሮ ሁለገብ የስፖርት ማሰልጠኛ እንዲሁም በመተከል ዞን ወምበራ አትሌቲክስ ማሰልጠኛ ማዕከሎች ይገነባሉ ብለዋል፡፡ የስፖርት ማሰልጠኛ ማዕከሎቹ በአጠቃላይ 361 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ወጪ እንደሚደረግባቸው ኮሚሽነሩ አመልክተዋል፡፡ ለግንባታ የሚውለው በጀት ከክልሉ መንግስት፣ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች፣ ከገቢ ማሰባሰቢያ ቴሌቶን፣ ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን፣ ከኢትዮጵያ ኦለምፒክ ኮሚቴ እና ከሌሎች አካላት እንደሚሰበሰብ አስረድተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የቴክኒክ፣ የሃብት አሰባሳቢ እና የቅስቀሳ ንዑስ ኮሚቴዎች ተደራጅተው ስራ መጀመራቸውን ኮሚሽነሩ ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት በስፖርት ማሰልጠኛ እጦት በክልሉ በተለይ በእግር ኳስ እና በአትሌቲክስ ስፖርቶች ብቃት ያላቸው ወጣቶች ተሰጧቸውን ማሳየት አለመቻላቸውን አስረድተዋል፡፡ የሚገነቡት ማሰልጠኛ ማዕከሎች በወቅቱ እንዲጠናቀቁ ህብረተሰቡን ጨምሮ ባለድርሻ አካላት ድጋፍ ሊጠናክር እንደሚገባ ጠይቀዋል፡፡ አትሌት አልማዝ አያና፣ አትሌት ጽጌ ዱጉማ፣ የቀድሞው የዋልያዎቹ አጥቂ ሳላሃዲን ሰይድ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የተገኙ ስፖርተኞች መሆናቸውን አስታውሰዋል።