ቀጥታ፡
ስፖርት
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ
Dec 18, 2025 56
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ መቻል ከድሬዳዋ ከተማ ይጫወታሉ። መቻል በሊጉ ባደረጋቸው 12 ጨዋታዎች ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ተሸንፏል። ሁለት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 20 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ሰባት ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ26 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 12 ጨዋታዎች መካከል አራቱን ሲያሸንፍ ሰባት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። 12 ግቦችን ሲያስቆጥር 18 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ድሬዳዋ በ13 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ጨዋታው መቻል ተከታታይ ድሎችን ለማስመዝገብ፣ ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር ሸገር ከተማ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በሊጉ 11 ጨዋታዎችን አድርጎ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። በጨዋታዎቹ 18 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 10 ጎሎችን አስተናግዷል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ሸገር ከተማ በ24 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው 12 ጨዋታዎች 12 ጨዋታዎች አምስቱን ሲያሸንፍ ሁለት ሽንፈት አጋጥሞታል። በአምስት ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይቷል። 13 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያስቆጥር 10 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ20 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ማንችስተር ሲቲ ለካራባኦ ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ አለፈ
Dec 18, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 8/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ብሬንትፎርድን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ራያን ቸርኪ በ32ኛው እና ሳቪኒዮ 67ኛው ደቂቃ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በጨዋታው ማንችስተር ሲቲ በተጋጣሚው ላይ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። የማንችስተር ሲቲው ተከላካይ አብዱኮዲር ኩሳኖቭ በ16ኛው ደቂቃ ላይ በብሬንትፎርዱ ኬቨን ሻደ የሰራው ጥፋት በቢጫ ካርድ መታለፉ አጨቃጫቂ ነበር። ሻደ የመጨረሻ ሰው ሆኖ በተሰራው ጥፋት ኩሳኖቭ በቀይ ካርድ መውጣት ነበረበት የሚል ተቃውሞ ብሬንትፎርዶች ቢያሰሙም ውሳኔው ሳይቀለበስ ቀርቷል። በካራባኦ ዋንጫ በቪዲዮ የታገዘ ዳኝነት (ቫር) የሚተገበረው ከግማሽ ፍጻሜ አንስቶ ነው። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ሲቲ ለካራቦኦ ግማሽ ፍጻሜ ሲያልፍ ከእ.አ.አ 2021 በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።   በሌላኛው መርሃ ግብር ኒውካስትል ዩናይትድ ፉልሃምን 2 ለ 1 አሸንፏል። ዮአን ዊሳ እና ሉዊስ ማይሊ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሳሳ ሉኪች ለፉልሃም ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የወቅቱ የካራባኦ ዋንጫ አሸናፊ ኒውካስትል ዩናይትድ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የግማሽ ፍጻሜ ድልድል ወጥቷል። ኒውካስትል ዩናይትድ ከማንችስተር ሲቲ እና ቼልሲ ከአርሰናል እና ክሪስታል ፓላስ አሸናፊ ጋር ይጫወታሉ። አርሰናል ከክሪስታል ፓላስ በዚህ ሳምንት ሊያደርጉት የነበረው ጨዋታ በመርሃ ግብር መደራረብ በመራዘሙ ምክንያት በቀጣዩ ሳምንት ማክሰኞ ይካሄዳል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ልደታ ክፍለ ከተማ አርባ ምንጭ ከተማን በማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና የወጣበትን ወሳኝ ድል አስመዘገበ 
Dec 17, 2025 85
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 8/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ልደታ ክፍለ ከተማ አርባ ምንጭ ከተማን 4 ለ 2 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሄለን እሸቱ፣ ረድኤት ዳንኤል እና ሰብለወንጌል ወዳጆ በጨዋታ፣ ቃልኪዳን ጥላሁን በፍጹም ቅጣት ምት ለልደታ ክፍለ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። መሰረት ማቴዎስ እና ፍሬህይወት በድሉ ለአርባ ምንጭ ከተማ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ልደታ ክፍለ ከተማ በስምንት ነጥብ ደረጃውን 13ኛ ወደ 14ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። በሊጉ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባ ምንጭ ከተማ በተመሳሳይ ስምንት ነጥብ ከነበረበት 12ኛ ደረጃ ወደ 13ኛ ዝቅ ማለት ወራጅ ቀጠና ገብቷል። ዛሬ በተደረጉ የ13ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ባህር ዳር ከተማ አዲስ አበባ ከተማን 2 ለ 0፣ ሲዳማ ቡና ይርጋ ጨፌ ቡናን 2 ለ 1 አሸንፈዋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል 
Dec 17, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 8/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይደረጋሉ። ባህር ዳር ከተማ ከአዲስ አበባ ከተማ ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 12 ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ ዘጠኝ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ወጥቷል። ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር 16 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በሰባት ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ካከናወናቸው 12 ጨዋታዎች መካከል አንዱን ብቻ ያሸነፈው አዲስ አበባ ከተማ ዘጠኝ ሽንፈቶችን አስተናግዷል። ሁለት ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይቷል። አምስት ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር 24 ግቦች ተቆጥረውበታል። አዲስ አበባ ከተማ በአምስት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው ባህር ዳር ከተማ ተከታታይ ድል ለማስመዝገብ፣ አዲስ አበባ ከተማ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት የሚያደርጉት ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና ከይርጋ ጨፌ ቡና ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሲዳማ ቡና በውድድር ዓመቱ 11 ጨዋታዎችን አድርጎ አራት ጨዋታዎችን ሲያሸንፍ በተመሳሳይ በአራቱ ተሸንፏል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 12 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 11 ጎሎችን አስተናግዷል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው ሲዳማ ቡና በ15 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ይርጋ ጨፌ ቡና በሊጉ ካካሄዳቸው 12 ጨዋታዎች መካከል አራቱን ሲያሸንፍ በስድስቱ ተሸንፎ አራት ጊዜ አቻ ወጥቷል። አራት ግቦችን ሲያስቆጥር 15 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዲስ አዳጊው ይርጋ ጨፌ ቡና በ10 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። የዕለቱ የመጨረሻ መርሃ ግብር ልደታ ክፍለ ከተማ እና አርባ ምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ያገናኛል። ልደታ ክፍለ ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው 12 ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በዘጠኙ ሽንፈት ሲያስተናግድ ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። በ12ቱ ጨዋታዎች ስምንት ግቦችን ሲያስቆጥር 23 ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው አርባ ምንጭ ከተማ በበኩሉ ከ12 የሊጉ ጨዋታዎች መካከል ሁለቱን ሲያሸንፍ ስምንት ጊዜ ተሸንፏል። ሁለት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። ሰባት ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 21 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አርባ ምንጭ ከተማ በስምንት ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት እስከ ታህሳስ 10 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ33 ነጥብ ሊጉን ይመራል። ዳግማዊት ሰለሞን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በ17 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እያመራች ነው። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ በዘጠኝ እና የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ማህሌት ምትኩ በስድስት ግቦች ይከተላሉ።
በካራባኦ ዋንጫ ሁለት ለግማሽ ፍጻሜ የሚያልፉ ክለቦች የሚለዩባቸው ጨዋታዎች ይደረጋሉ 
Dec 17, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 8/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ካፕ ዛሬ ሁለት የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ ማንችስተር ሲቲ ከብሬንትፎርድ በኢትሃድ ስታዲየም ይጫወታሉ። ማንችስተር ሲቲ በአራተኛው ዙር ስዋንሲ ሲቲን 3 ለ 1 ማሸነፉ ይታወቃል። ተጋጣሚው ብሬንትፎርድ በበኩሉ ግሪምስቢ ታውንን 5 ለ 0 በመርታት ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ማንችስተር ሲቲ የካራባኦ ዋንጫን ስምንት ጊዜ በማንሳት ከስኬታማ ክለቦች ውስጥ የሚጠቀስ ነው። ብሬንትፎርድ በውድድር ተሳትፎ ታሪኩ ለፍጻሜ ደርሶ አያውቅም ። በሌላኛው መርሃ ግብር ኒውካስትል ዩናይትድ ከፉልሃም ምሽት 5 ሰዓት ከ15 ላይ በሴይንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኒውካስትል ዩናይትድ በአራተኛው ዙር ቶተንሃም ሆትስፐርስን 2 ለ 0 ረቷል። ፉልሃም ዋይኮምብን በመለያት ምት ማሸነፍ ችሏል። ኒውካስትል የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ነው። ቡድኑ የዋንጫ ክብሩን ለማስጠበቅ የለንደኑን ተጋጣሚውን ማሸነፍ ይኖርበታል። ፉልሃም የካራቦ ዋንጫን አንስቶ አያውቅም። ትናንት በተደረገ የመጀመሪያ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ ቼልሲ ካርዲፍ ሲቲን 3 ለ 1 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ ያለፈ የመጀመሪያው ክለብ ሆኗል።
ቼልሲ ለካራባኦ ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ ያለፈ የመጀመሪያ ቡድን ሆኗል
Dec 17, 2025 88
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 7/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ዋንጫ የመጀመሪያ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ቼልሲ ካርዲፍ ሲቲን 3 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በካርዲፍ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኤሌሃንድሮ ጋርናቾ በ57ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ቼልሲ መሪ ሆኗል። ዴቪድ ተርንቡል በ75ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ካርዲፍ አቻ አድርጓል። ፔድሮ ኔቶ በ82ኛው ደቂቃ ቼልሲን ሁለተኛውን ጎል አስቆጥሯል። ጋርናቾ ለራሱ ሁለተኛውን ለቡድኑ ሶስተኛውን ግብ በ93ኛው ደቂቃ ላይ ከመረብ ጋር አገናኝቷል። የምዕራብ ለንደኑ ቼልሲ በጨዋታው አብዛኛውን ቋሚ ተሰላፊዎቹን ተቀያሪ ወንበር ላይ አስቀምጦ የጀመረ ሲሆን ከእረፍት መልስ ተጫዋቾቹን ቀይሮ በማስገባት ውጤት ይዞ ወጥቷል። በእንግሊዝ ሶስተኛ የሊግ እርከን ሊግ አንድ የሚገኘው የዌልሱ ካርዲፍ ሲቲ ቼልሲን ቢፈትንም ማሸነፍ አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ ቼልሲ ለካራባኦ ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ ያለፈ የመጀመሪያ ቡድን ሆኗል። የካራባኦ ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ነገም ቀጥሎ ሲውል ማንችስተር ሲቲ ከብሬንትፎርድ እና የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ኒውካስትል ዩናይትድ ከፉልሃም ይጫወታሉ። አርሰናል ከክሪስታል ፓላስ በዚህ ሳምንት ሊያደርጉት የነበረው ጨዋታ በመርሃ ግብር መደራረብ ምክንያት ለቀጣዩ ሳምንት ተራዝሟል።
የ2018 ዓ.ም የልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክስ የውድድር ዘመን ዛሬ በይፋ ተጀመረ   
Dec 16, 2025 106
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 7/2018(ኢዜአ)፦ የቱሪዝም ዘርፉን የማስተዋወቅ አላማ ያለው የ2018 ዓ.ም የልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክስ የውድድር መርሃ ግብር ዛሬ ይፋ ሆኗል። የውድድር መርሃ ግብሩ ዘንድሮ የደብረ ብርሃን እና ሐረር ከተሞችን አካቷል። ይህ ስፖርት እና ቱሪዝምን በማቀናጀት የኢትዮጵያን ከተሞች እና የቱሪዝም ስፍራዎችን በስፋት እያስተዋወቀ የሚገኘው መርሃ ግብር አዳዲስ ከተሞችን በመጨመር ለሁለተኛ ተከታታይ ዓመት የሚካሔድ ሲሆን ከጥር እስከ ሐምሌ ፤ ከአንኮበር እስከ ሐረር በር በመሪ ሀሳብ ይከናወናል። ልወቅሽ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ትውልዱ ስለ ሀገሩ ባህል፣ ታሪክ እና የቱሪዝም መዳረሻዎች እንዲያውቅ ለማድረግ ያለመ ንቅናቄ ነው። ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በተለያዩ ከተሞች የ"ልወቅሽ ኢትዮጵያ" የሩጫ ውድድር ባለፉት ዓመታት እየተካሄደ ይገኛል። ዘንድሮም ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ከቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክስ በሚል ስያሜ በስድስት የክልል ከተማዎች ላይ ተከታታይ የሩጫ ውድድር እንደሚያዘጋጅ አስታውቋል።   በ2017 ዓ.ም በአራት መዳረሻ ከተማዎች ላይ የተካሄደው የልወቅሽ ኢትዮጵያ ክላሲክስ ተከታታይ ውድድር ፤ በዚህም ዓመት ደብረብርሃን እና ሐረርን በመጨመር ስድስት ከተማዎች ላይ ይካሄዳል። ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ባለፈውም ዓመት አዘጋጅ በነበሩት ሃዋሳ፣ ጅማ፣ በቆጂ እና አርባምንጭ ላይ ለተከታታይ ዓመታት ያደረገ ሲሆን ዘንድሮም ውድድሩን ለማካሄድ ተዘጋጅቷል። የቱሪዝም ሚኒስቴር እና ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ስፖርት እና ቱሪዝምን በማስተሳሰር እየሰሯቸው ያሉትን ስራዎች ይበልጥ አጠናክሮ ለመስራት የሚያስችላቸው የመግባቢያ ሰነድ ዛሬ ተፈራርመዋል። የቱሪዝም ሚኒስትር ዲኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር) ልወቅሽ ኢትዮጵያ ኢትዮጵያንን ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ሀገራት ተሳታፊዎችን መሳብ የቻለ ዝግጅት ለመሆን መብቃቱን ገልጸዋል። የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዲኤታ መኪዩ መሃመድ በበኩላቸው “ስፖርትን ከቱሪዝም ጋር በማጣመር ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ እየሰራ ያለውን ስራ አድንቀዋል። መንግስት ልወቅሽ ኢትዮጵያ ውድድር እንዲሰፋ ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ጋር በትብብር ይሰራል ብለዋል።   የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ስራ አስኪያጅ ዳግማዊት አማረ በበኩላቸው፤ ‘ልወቅሽ ኢትዮጵያ’ የሚል አዲስ የቱሪዝም ምርት በማስተዋወቃችን እና ከሩጫ ውድድርነት ባሻገር ኢትዮጵያን በትንሹም ቢሆን ማሳየት በመቻላችን ደስተኞች ነን ሲሉ ገልጸዋል። መንግስት ንቅናቄው እና ውድድሩ እንዲሳካ ላደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። የልወቅሽ ኢትዮጵያ በደብረ ብርሃን ከተማ ጥር 3 ቀን 2018 ዓ.ም. የማራቶን ዱላ ቅብብል እና የሀገር አቋራጭ ውድድሮችን በማካተት ጅማሮውን ያደርጋል። መርሃ ግብሩ ከሩጫው ባሻገር ልዩ የጉብኝት ፓኬጆችን በማዘጋጀት ዜጎች የተፈጥሮና የቅርስ ስፍራዎችን እንዲጎበኙ እያስቻለ ይገኛል።
በካራባኦ ዋንጫ ካርዲፍ ሲቲ ከቼልሲ ጋር ይጫወታል
Dec 16, 2025 104
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ካፕ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ካርዲፍ ሲቲ ከቼልሲ ጋር ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በካርዲፍ ስታዲየም ይካሄዳል። ካርዲፍ ሲቲ በአራተኛው ዙር ሬክሳምን 2 ለ 1 አሸንፏል። ቼልሲ ዎልቭስን 4 ለ 3 ረቷል። የዌልሱ ክለብ ካርዲፍ ሲቲ የካራባኦ ዋንጫን አንስቶ አያውቅም። እ.አ.አ በ2011/12 ለፍጻሜ ደርሶ በሊቨርፑል የተሸነፈ ሲሆን ብቸኛው ለዋንጫው የተጠጋበት አጋጣሚም ነበር። የምዕራብ ለንደኑ ክለብ ቼልሲ አምስት ጊዜ የካራባኦ ዋንጫን አንስቷል። ቡድኑ ለመጨረሻ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ የነበረው እ.አ.አ በ2014/15 ነበር። የካራባኦ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ነገም ሲቀጥል ማንችስተር ሲቲ ከብሬንትፎርድ እና ኒውካስትል ዩናይትድ ከፉልሃም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በዚህ ሳምንት ሊደረግ የነበረው የአርሰናል እና ክሪስታል ፓላስ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ ክሪስታል ፓላስ ተደራራቢ ጨዋታዎች ስለበዙብኝ ይራዘምልኝ ብሎ ለአወዳዳሪው አካል ባቀረበው ጥያቄ መሰረት ወደ ቀጣዩ ሳምንት ተሸጋግሯል። እ.አ.አ በ1960 የተጀመረው የካራባኦ ካፕ (በቀድሞ አጠራሩ የእንግሊዝ ፉትቦል ሊግ ዋንጫ) በእንግሊዝ ከአንጋፋው ኤፍ ካፕ ውጪ የሚደረገው የጥሎ ማለፍ ውድድር ነው። ሊቨርፑል 10 ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት የውድድሩ ስኬታማ ክለብ ነው። ማንችስተር ሲቲ ስምንት እና ማንችስተር ዩናይትድ ስድስት ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ ይከተላሉ።
ስምንት ግቦች በተቆጠሩበት አዝናኝ ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ እና ቦርንማውዝ አቻ ተለያዩ
Dec 16, 2025 121
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 6/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ16ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር ማንችስተር ዩናይትድ እና ቦርንማውዝ አራት አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አማድ ዲያሎ፣ ካሲሚሮ፣ ብሩኖ ፈርናንዴዝ እና ማትያስ ኩንሃ ለማንችስተር ዩናይትድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አንቶዋን ሴሜንዮ፣ ኢቫኒልሰን፣ ማርከስ ታቫርኒየር እና ጁኒየር ክሩፒ ለቦርንማውዝ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ማንችስተር ዩናይትድ በጨዋታው ሶስት ጊዜ መምራት ቢችልም ውጤቱን ማስጠበቅ አለመቻሉ ዋጋ አስከፍሎታል። ጨዋታው ተመጣጣኝ እና አዝናኝ ፉክክር ታይቶበታል። የሁለቱ ቡድኖች የተከላካይ ክፍል መስመር ተጋላጭነትም በግልጽ ለመመልከት ተችሏል። በጨዋታው ከ30 በላይ የግብ ሙከራዎች ተደርገዋል። ውጤቱን ተከቶሎ ማንችስተር ዩናይትድ በ26 ነጥብ ደረጃውን ከስምንተኛ ወደ ስድስተኛ ከፍ አድርጓል። ቦርንማውዝ በ21 ነጥብ ደረጃውን ከ15ኛ ወደ 13ኛ ከፍ ማድረግ ችሏል። ቡድኑ ባለፉት ሰባት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም።
በክልሉ ብቁና ውጤታማ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Dec 15, 2025 116
ባሕር ዳር ፤ ታሕሳስ 6/2018 (ኢዜአ) ፡- በአማራ ክልል በሁሉም የስፖርት ዘርፍ ብቁና ተወዳዳሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት በመከናወን ላይ እንደሚገኙ የክልሉ ባሕል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ገለጸ። ከሲዳማ ክልል የተለያዩ ተቋማት የተውጣጡ አመራርና አባላት የባሕር ዳር ዓለም ዓቀፍ ስታዲዮም የማጠናቀቂያ ስራዎችን በመጎብኘት የልምድና ተሞክሮ ልውውጥ አድርገዋል። የአማራ ክልል ባሕል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ መልካሙ ፀጋዬ በወቅቱ በተለይ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ከለውጡ ወዲህ ለስፖርት ዘርፉ በተሰጠው ልዩ ትኩረት ታዳጊዎች ላይ መሰረት ተደርጎ እየተሰራ ነው።   ለዚህም በተለያዩ አካባቢዎች ከ90 በላይ የስፖርት ማዘውተሪያ ማዕከላትና ፕሮጀክቶች መቋቋማቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም በእግር ኳስና በአትሌቲክስ ላይ ሰፊ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ለፕሮጀክቶች ውጤታማነት ክትትልና ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህም ክልሉን ብሎም ሃገርን የሚወክሉ ብቁና ውጤታማ ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ተግባሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል። ቀደም ሲል በተከናወኑ ተግባራት በዘርፉ ተጨባጭ ውጤት እየተገኘ መሆኑን ጠቅሰው፤ በደባርቅ፣ በደብረብርሃን፣ በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲና ሌሎች አካባቢዎች በተቋቋሙ ፕሮጀክቶች ከታቀፉ ታዳጊዎች አትሌቶችና የእግር ኳስ ተጨዋቾችን ማፍራት እንደተቻለም ለአብነት አንስተዋል። ከሲዳማ ክልል የመጡት አመራርና አባላትም በባሕር ዳር ዓለም ዓቀፍ ስታዲዮም የካፍና የፊፋን ደረጃ ባሟላ መልኩ እየተከናወኑ የሚገኙ የማጠናቀቂያ ስራዎችን ተመልክተው ልምድና ተሞክሮ ለመውሰድ መሆኑን ተናግረዋል።   የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የጎብኚዎቹ ቡድኑ መሪ አቶ ካሱ አሩሳ በበኩላቸው፤ አመራርና አባላቱ ከክልሉ የተለያዩ ተቋማት ተወክለው እንደመጡ ጠቅሰው፤ በዚህም የባሕርዳር ዓለም አቀፍ ስታዲዮምን የስራ ሁኔታ በመመልከት ልምድና ተሞክሮ ማግኘታቸውን ገልጸዋል። የባሕር ዳር ስታዲዮም ዘመኑን የዋጁ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የካፍና የፊፋን ደረጃዎች ባሟላ መልኩ የተገነባ መሆኑን እንደተረዱ ተናግረዋል። የሀዋሳ ስታዲዮም ዓለም አቀፍ ደረጃውን ባሟላ መልኩ መገንባት የሚያስችል ልምድ ማግኘታቸውን የተናገሩት ደግሞ የሲዳማ ክልል ባሕል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃጎ አገኘሁ ናቸው።   ከስታዲዮሙ አጥር ጀምሮ የሳር ተከላ፣ የ"ቪ አይ ፒ " መግቢያዎች፣ መቀመጫዎች፣ የተጫዋቾች ማረፊያ፣ የመልበሻና ሌሎችም መገልገያዎች የካፍና የፊፋን ደረጃ ባሟላ መልኩ መገንባቱን እንደተረዱ ገልጸዋል። አጠቃላይ የተመለከቷቸውን የማጠናቀቂያ ስራዎች ልምድና ተሞክሮ ወስደው የሃዋሳ ዓለም አቀፍ ስታዲዮም ላይ እንደሚተገብሩትም አንስተዋል።      
በፕሪሚየር ሊጉ ማንችስተር ዩናይትድ ከቦርንማውዝ ይጫወታል 
Dec 15, 2025 146
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 6/2018(ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር በማንችስተር ዩናይትድ እና ቦርንማውዝ መካከል ዛሬ ይካሄዳል። ጨዋታው ምሽት 5 ሰዓት ላይ በኦልትራፎርድ ስታዲየም ይደረጋል። ማንችስተር ዩናይትድ በ25 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ቦርንማውዝ በ20 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ17ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 16 ጨዋታዎች ማንችስተር ዩናይትድ ዘጠኝ ጊዜ ሲያሸንፍ ቦርንማውዝ አራት ጊዜ ድል ቀንቶታል። ሶስት ጊዜ አቻ ወጥተዋል። ማንችስተር ዩናይትድ በጨዋታዎቹ ላይ 30 ግቦችን ሲያስቆጥር ቦርንማውዝ 18 ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፏል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች በነበራቸው የእርስ በእርስ ግንኙነት ቦርንማውዝ ሁለት ጨዋታዎችን ሲያሸንፍ ማንችስተር ዩናይትድ አንድ ጊዜ አሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርተዋል። ሁለቱ ቡድኖች በጨዋታው ላይ ተመጣጣኝ ፋክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። የ43 ዓመቱ ሳይመን ሁፐር ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ተጠባቂ ጨዋታ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን አሸነፈ
Dec 14, 2025 137
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ማህሌት ምትኩ በ35ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። በጨዋታው ላይ ድንቅ ብቃቷን ያሳየችው ማህሌት ምትኩ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በውድድር ዓመቱ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ነጥቡን ወደ 33 ከፍ አድርጓል። በሊጉ የመጀመሪያ ሽንፈቱን ያስተናገደው የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታዎች እየቀሩት በ25 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረገ ሌላኛው ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ እና አዳማ ከተማ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ13ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከታህሳስ 8 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እንደሚካሄዱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
በሊጉ ተጠባቂ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ክሪስታል ፓላስን አሸንፏል
Dec 14, 2025 119
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ክሪስታል ፓላስን 3 ለ 0 አሸንፏል። በስልኸረስት ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሊንግ ሃላንድ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ፊል ፎደን ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የጨዋታው ኮከብ ሆኖ የተመረጠው ሃላንድ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ 17 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን አጠናክሯል። በሊጉ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ ነጥቡን ወደ 34 ከፍ በማድረግ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ክሪስታል ፓላስ በ26 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች አስቶንቪላ ዌስትሃም ዩናይትድን 3 ለ 2 በማሸነፍ በ33 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ኖቲንግሃም ፎረስት ቶተንሃም ሆትስፐርስን 3 ለ 0፣ ሰንደርላንድ ኒውካስትል ዩናይትድን 1 ለ ዐ አሸንፈዋል። ብሬንትፎርድ እና ሊድስ ዩናይትድ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። የ16ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር በማንችስተር ዩናይትድ እና ቦርንማውዝ መካከል ነገ ይደረጋል።
ሲዳማ ቡና እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ለኢትዮጵያ ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ አለፉ
Dec 14, 2025 102
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሶስተኛ ዙር የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገዋል። በአዳስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሲዳማ ቡና አርባምንጭ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ፍቅረየሱስ ተክለብርሃን እና ብሌዝ ናጎ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ንብ እግር ኳስ ክለብን 2 ለ 1 አሸንፏል። ያሬድ ከበደ በጨዋታ እና ጌትነት ተስፋዬ በቀለም ቅጣት ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ኢዮብ ደረሰ ለንብ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቶቹን ተከትሎ ሲዳማ ቡና እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ለሩብ ፍጻሜ አልፈዋል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ ቤንች ማጂ ቡና ደብረብርሃን ከተማን በመለያ ምት አሸንፎ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅለዋል። ኢትዮጵያ መድን፣ መቻል፣ ነጌሌ አርሲ እና ቦዲቲ ከተማ ሌሎች ለሩብ ፍጻሜ ያለፉ ክለቦች ናቸው። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር የመጨረሻ መርሃ ግብር ነገ በኢትዮጵያ ቡና እና መቀሌ 70 እንደርታ መካከል በአዲስ አበባ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ይደረጋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም