ቀጥታ፡
ስፖርት
ብቁና ተፎካካሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Nov 17, 2025 40
ባሕርዳር፤ ሕዳር 8/2018(ኢዜአ)፡- በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ መድረክ የሚወክሉ ብቁና ተፎካካሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ባሕልና ስፖርት ሚኒስትር ሽዊት ሻንካ ገለጹ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና ማሕበራዊ ልማት፣ ባሕልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት የባሕር ዳር ስታዲየምን እየጎበኙ ነው። በጉብኝቱ ላይ የተገኙት የባሕልና ስፖርት ሚኒስትር ሽዊት ሻንካ እንደተናገሩት፤ ለስፖርት ዘርፍ እድገት በትኩረት እየተሰራ ነው። ይህም እግር ኳስን ጨምሮ በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ኢትዮጵያን ወክለው በዓለም አቀፍ መድረክ ብቁ ተፎካካሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ከእነዚህም ደረጃቸውን ጠብቀው እየተከናወኑ ያሉ ታላላቅ፣ መካከለኛና አነስተኛ ስታድየሞች ግንባታን ጠቅሰዋል።   ይህም ታዳጊና ህፃናትን መሰረት ያደረገ እንደሆነ ጠቁመው፤ ተግባሩ ይበልጥ ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ አረጋግጠዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና ማሕበራዊ ልማት፣ ባሕልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ታደለ ቡራቃ(ዶ/ር) በበኩላቸው፣ በሀገሪቱ ብቁ ስፖርተኞችን ለማፍራት ህፃናትና ታዳጊዎች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ማረጋገጥ ችለናል ብለዋል። በሁሉም አካባቢዎች እየተገነቡ የሚገኙ ስታድየሞች ደረጃቸው ከፍ ያለና የሀገሪቱን የስፖርት ዘርፍ እድገት ለማላቅ የሚያግዙ እንደሆኑም ገልጸዋል። የዛሬው ምልከታም ለተወካዮች ምክር ቤት የሚቀርቡ የዘርፉን ሪፖርቶች ትክክለኛነት ያረጋገጥንበት ነው ብለዋል። የአማራ ክልል ርዕስ መስተዳድር የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ እርዚቅ ኢሣ ፤ የባሕርዳር ስታድየም የፊፉን እና ካፍን መስፈርቶች ማሟላት በሚችል አግባብ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   ስታዲዮሙ እግር ኳስን ጨምሮ ሌሎች 23 የስፖርት ዓይነቶችን ማስተናገድ እንዲችል ሆኖ የጥራት ደረጃውን ጠብቆ በመገንባት ላይ እንደሚገኝ አብራርተዋል። የስታድየሙ አብዛኛው ስራ እየተጠናቀቀ መሆኑንና ቀሪዎቹን ፈጥኖ ለመፈፀም ርብርብ እየተደረገ መሆኑም ተመላክቷል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና ማሕበራዊ ልማት፣ ባሕልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት ከስታዲየሙ በተጨማሪ የዕደ ጥበብ ማዕከላት፤ የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቴክስታይልና ፋሽን ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት እንደሚጎበኙ ይጠበቃል፡፡
በሊጉ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ መድን የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው 
Nov 16, 2025 79
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 7/ 2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ መድን ዛሬ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል። በአዲስ አበባ ስታዲየም የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና የወቅቱ የሊጉ ዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን የሚያደርጉት ጨዋታ የተመልካቾችን ትኩረት ስቧል።   ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈትን አስተናግዷል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቡዱኑ በዘጠኝ ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ መድን በበኩሉ በውድድር ዓመቱ ባደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ድል ሲቀናው ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ አንድ ግብ ተቀጥሮበታል። መድን በአምስት ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።   ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። ሁለቱ ቡድኖች በ2017 ዓ.ም በሊጉ ያደረጓቸው ሁለት ጨዋታዎች በተመሳሳይ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል። የቡድኖች ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ከግብጹ ፒራሚድስ ጋር በነበረው የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ ምክንያት የተራዘመ ነው። ኢትዮጵያ መድን በቀጣይ በሚገለጽ ቀን እና ቦታ ከሸገር ከተማ ጋር ቀሪውን ተስተካካይ ጨዋታ እንደሚያደርግ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል  
Nov 16, 2025 58
አዲስ አበባ፤ ህዳር 7/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከልደታ ክፍለ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ያደረጋቸውን ሶስት ጨዋታዎች አሸንፏል። በጨዋታዎቹ 12 ጎሎችን ሲያስቆጥር የተቆጠረበት አንድ ግብ ብቻ ነው። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ የሆነው ንግድ ባንክ በዘጠኝ ነጥብ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በዘጠኝ ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ልደታ ክፍለ ከተማ በውድድር ዓመቱ ካካሄዳቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ በተመሳሳይ በሁለት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።   በሌላኛው መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባህር ዳር በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው ። በሶስት ጨዋታዎች ሽንፈት ሲያስተናግድ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አምስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በሶስት ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ እስከ አሁን ባደረገው አራት ጨዋታ ማሸነፍ አልቻለም። ሶስት ጊዜ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ አምስት ግብ ሲቆጠርበት ምንም ጎል አላስቆጠረም። አርባምንጭ ከተማ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዛለች።
ኢትዮጵያ የምታዘጋጀው የሴካፋ ዞን ከ17 ዓመት በታች አፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ  ይጀመራል ዛሬ ይጀመራል   
Nov 15, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ዛሬ ይጀመራል። የአፍሪካ ዋንጫው እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይከናወናል። በውድድሩ ላይ የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ የእግር ኳስ ማህበራት ምክር ቤት(ሴካፋ) ዞንን ወክለው የሚሳተፉ ሁለት ሀገራት የሚለዩበት የማጣሪያ ውድድር በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል። ሴካፋ የማጣሪያ ውድድሩ የምድብ ድልድል ከሁለት ሳምንት ገደማ በፊት በዩጋንዳ ይፋ ማድረጉ የሚታወስ ነው። በምድብ አንድ አዘጋጇ ኢትዮጵያ ከሶማሊያ፣ ኬንያ፣ ደቡብ ሱዳን እና ሩዋንዳ ጋር ተደልድላለች። ዩጋንዳ፣ ታንዛንያ፣ ጅቡቲ፣ ሱዳን እና ብሩንዲ በምድብ ሁለት የተደለደሉ ሀገራት ናቸው። ውድድሩ በአበበ ቢቂላ እና ድሬዳዋ ኢንተርናሽናል ስታዲየሞች ይካሄዳል።   ቡድኖቹ አዲስ አበባ ከገቡ በኋላ የእድሜ ተገቢነት (MRI) ምርመራ በማከናወን ዩጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ታንዛንያ፣ ሱዳን እና ጅቡቲ የምድብ ጨዋታቸውን ወደ ሚያደርጉበት ድሬዳዋ ያመሩ ሲሆን ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሶማሊያ እና ሩዋንዳ ደግሞ የምድብ ጨዋታቸውን አዲስ አበባ አበበ ቢቂላ ስታዲየም ላይ የሚያከናውኑ ይሆናል። ዛሬ አዘጋጇ ኢትዮጵያ ከሩዋንዳ ከቀኑ 10 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሶማሊያ ከደቡብ ሱዳን ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ የሚያደርጉት ጨዋታ የመክፈቻ መርሃ ግብር ይሆናል። በድሬዳዋ ኢንተርናሽናል ስታዲየም ታንዛንያ ከሱዳን ከቀኑ 11 ሰዓት፣ ብሩንዲ ከዩጋንዳ ከምሽቱ 2 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን የሴካፋ ዞን ከ17 ዓመት በታች አፍሪካ ዋንጫ የማጣርያ ውድድር ዝግጅቱን በአዲስ አበባ ሲያደርግ ቆይቷል። ብሄራዊ ቡድኑ የሚሰለጥነው በአሜሪካዊው ቤንጃሚን ዚመር ነው። ተጫዋቾቹ የተመለመሉት ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2026 የሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ለማስተናገድ ያቀረበችው ጥያቄ አካል የሆነው የ"Road to 2029" ፕሮጀክት የ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ካምፒንግ መሆኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የሴካፋ ዞን ማጣሪያ እስከ ህዳር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በማጣሪያው ለፍጻሜ የሚያልፉት ሁለት ሀገራት የሴካፋ ዞንን ወክለው ለአፍሪካ ዋንጫ ያልፋሉ። እ.አ.አ በ2026 በሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጇ ሞሮኮን ጨምሮ 16 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ መሪነቱን ያጠናከረበትን ድል አስመዘገበ 
Nov 14, 2025 73
አዲስ አበባ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሃ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሃዋሳ ከተማን 3 ለ 2 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳግማዊት ሰለሞን በጨዋታ እና ፍጹም ቅጣት ምት ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር ማህሌት ምትኩ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ፀሐይነሽ ጁላ እና የምስራች ላቀው ለሃዋሳ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ማህሌት ምትኩ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ድሉን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ18 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ሃዋሳ ከተማ በ12 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን በሊጉ ከመረብ ላይ ያሳረፈቻቸውን ግቦች ወደ 11 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቷን አጠናክራለች። በአሁኑ ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ሲዳማ ቡና ከአዲስ አበባ ከተማ ጋር ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል።
የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሃዋሳ ከተማ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል 
Nov 14, 2025 113
አዲስ አበባ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሁለት ጨዋታዎች በአበባ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ሃዋሳ ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ይጫወታሉ። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አራት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በጨዋታዎቹ ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ በሊጉ ያከናወናቸውን አምስት ጨዋታዎች አሸንፏል። 13 ግቦችን ሲያስቆጥር የተቆጠረበት አንድ ግብ ብቻ ነው። ቡድኑ በ15 ነጥብ ሊጉን እየመራ ይገኛል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት ጥሩ ጅማሮ ያሳዩት ሁለቱ ክለቦች በጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና ከአዲስ አበባ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሲዳማ ቡና በሊጉ ካደረጋቸው አራት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ሲዳማ ቡና አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በስድስት ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል አንዱን ሲያሸንፍ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በጨዋታዎቹ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር 11 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በሶስት ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ቀሪ ስምንት ክለቦች ቀጣዩን ዙር ተቀላቅለዋል 
Nov 13, 2025 104
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና አዳማ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። አቡበከር አዳሙ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። አህመድ ሁሴን ለአዳማ ከተማ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ባህር ዳር ከተማ ሸገር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አማኑኤል ገብረሚካኤል እና ግርማ ዲሳሳ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ በሬድዋን ሸረፋ ግብ ሃዋሳ ከተማን 1 ለ 0 ረቷል።   በተመሳሳይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን በመለያ ምት 4 ለ 2 አሸንፏል። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል። በሌሎች ጨዋታዎች አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ 2 ለ 1 እና ቢሾፍቱ ከተማ ደሴ ከተማን 1 ለ 0 ሲያሸንፉ ንብ እግር ኳስ ክለብ የካ ክፍለ ከተማን ደብረብርሃን ከተማ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማን በመለያ ምት ማሸነፍ ችለዋል። ዛሬ እና ትናንት የተደረጉ ጨዋታዎችን ተከትሎ 16 ክለቦች ለሶስተኛው ዙር አልፈዋል።   ኢትዮጵያ መድን፣ ቤንች ማጂ ቡና፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ፣ አርባምንጭ ከተማ፣ ቦዲቲ ከተማ፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ መቻል፣ ነጌሌ አርሲ፣ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ፣ ድሬዳዋ ከተማ፣ ባህር ዳር ከተማ፣ ደብረብርሃን ከተማ፣ ንብ እግር ኳስ ክለብ፣ ቢሾፍቱ ከተማ፣ ኢትዮጵያ ቡና እና ሲዳማ ቡና 16ቱን የተቀላቀሉ ክለቦች ናቸው። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ ከውድድሩ ተሰናብቷል። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር በቀጣይ በሚገለጽ ቀን እና ቦታ ይካሄዳል።
መቻል፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ ነጌሌ አርሲ እና ቦዲቲ ከተማ በኢትዮጵያ ዋንጫ ወደ ሶስተኛ ዙር አለፉ
Nov 13, 2025 88
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ጨዋታዎች ዛሬም እየተካሄዱ ነው። በሃዋሳ አርቴፊሻል ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ መቻል ምድረገነት ሽሬን 3 ለ 0 አሸንፏል። አብዱልከሪም ወርቁ በጨዋታ፣ ዮሴፍ ታረቀኝ በፍጹም ቅጣት እና የምድረገነት ሽሬው ክብሮም ብርሃነ በራሱ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሌላኛው መርሃ ገብር ነጌሌ አርሲ ሀዲያ ሆሳዕናን በመለያት ምት 8 ለ 7 አሸንፏል። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሀቢብ ከማል ለነጌሌ አርሲ፣ ብሩክ በየነ ለሀዲያ ሆሳዕና ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ ፋሲል ከነማን በአሸናፊ ሀፍቱ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል። ቦዲቲ ከተማ ሃላባ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በጅማ ስታዲየም በተደደረገው ጨዋታ አጥናፉ ቡሸና የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። መቻል፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ ነጌሌ አርሲ እና ቦዲቲ ከተማ 16ቱን ተቀላቅለዋል። ቀሪ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች ዛሬ ከሰዓት በኋላ ይካሄዳሉ። ትናንት በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን፣ አርባምንጭ ከተማ፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ቤንጅ ማጂ ቡና ወደ ሶስተኛ ዙር ማለፋቸው ይታወቃል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ ሁለተኛ ዙር ቀሪ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ 
Nov 13, 2025 99
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ዛሬ 12 ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየም ሀዲያ ሆሳዕና ከነጌሌ አርሲ ከረፋዱ 4 ሰዓት፣ ባህር ዳር ከተማ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና አዳማ ከተማ ከኢትዮጵያ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ። ምድረገነት ሽሬ ከመቻል ከረፋዱ 4 ሰዓት፣ ሐረር ከተማ ከአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ንብ እግር ኳስ ክለብ ከየካ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት በሃዋሳ አርቴፊሻል ስታዲየም የሚካሄዱ ጨዋታዎች ናቸው። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም መቀሌ 70 እንደርታ ከፋሲል ከነማ ከረፋዱ 4 ሰዓት፣ ድሬዳዋ ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። ሃላባ ከተማ ከቦዲቲ ከተማ ከቀኑ 4 ሰዓት፣ ደብረብርሃን ከተማ ከአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ቢሾፍቱ ከተማ ከደሴ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት በጅማ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ትናንት በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን፣ አርባምንጭ ከተማ፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ቤንጅ ማጂ ቡና ወደ ሶስተኛ ዙር ማለፋቸው ይታወቃል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ በወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የ2 ለ 0 አስተናግዶ ከኢትዮጵያ ዋንጫ ተሰናብቷል። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሚያሸንፍ ቡድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ
Nov 13, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት መቻል ከይርጋጨፌ ቡና ይጫወታሉ። መቻል በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። አንድ ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በ10 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በውድድር ዓመቱ ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አንድ ጨዋታ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ ነጥብ ተጋርቷል። ይርጋጨፌ በአራት ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። መቻል በአምስተኛ ሳምንት አርባምንጭ ከተማን 2 ለ 0 ሲያሸንፍ ይርጋጨፌ ቡና ከአዳማ ከተማ አንድ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር አዳማ ከተማ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዳማ ከተማ በሊጉ ባካሄዳቸው አምስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ አሸንፎ ሶስት ጊዜ ተሸንፎ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በአራት ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል በሁለቱ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። ቡድኑ በስድስት ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። በአምስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር አዳማ ከተማ ከይርጋጨፌ ቡና አንድ አቻ ሲለያይ ቦሌ ክፍለ ከተማ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የ3 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም