ስፖርት
ፋሲል ከነማ እና መቻል አቻ ተለያዩ 
Jan 21, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2017 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ፋሲል ከነማ እና መቻል ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በረከት ደስታ በ38ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል መቻልን መሪ አድርጋ ነበር። ይሁንና ከእረፍት መልስ አንዋር ሙራድ በ70ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ለፋሲል ከነማ አንድ ነጥብ አስገኝታለች። ውጤቱን ተከትሎ መቻል በ26 ነጥብ ተመሳሳይ ነጥብ ባለው የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። መቻል ዳግም የሊጉን መሪነት መረከብ የሚችልበትን እድል ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ፋሲል ከነማ በ17 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቀን ላይ በተደረገ ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ አንድ አቻ ተለያይተዋል። የዛሬ ጨዋታዎችን ተከትሎ የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ16ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከአንድ ቀን እረፍት በኋላ ከጥር 15 ቀን 2017 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳሉ።
መቻል ከፋሲል ከነማ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 21, 2025 59
አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 15ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ መቻል ከፋሲል ከነማ የሚያደርጉት ጨዋታ የተመልካችን ቀልብ የሳበ ሆኗል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። መቻል በሊጉ ካደረጋቸው ያለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች መካከል ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ወጥተዋል። በጨዋታዎቹ ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር አምስት ጎሎችን አስተናግዷል። መቻል በ25 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። ሁለት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። በአምስቱ ጨዋታዎች ሶስት ጎሎችን ሲያስቆጥር ሁለት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ16 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። መቻል የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፈ ዳግም ወደ ሊጉ መሪነት ይመለሳል። በሌላኛው የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር በወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኙት ሃዋሳ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው ያለፉት አምስት ተከታታይ ጨዋታዎች መካከል በሶስቱ ሲሸነፍ ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። ቡድኑ በአምስቱ ጨዋታዎች ምንም ግብ አላስቆጠረም። በአንጻሩ አራት ጎችን አስተናግዷል። ሃዋሳ ከተማ በ17 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በበኩሉ ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ውስጥ አራት ጊዜ ሲሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በአምስቱ ጨዋታዎች ምንም ጎል ሳያስቆጥር ሲቀር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በአንድ ነጥብ የመጨረሻው 18ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቡድኑ እስከ አሁን በሊጉ ያላሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው። በተያያዘ ዜና ትናንት በተደረጉ የ15ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች ሀዲያ ሆሳዕና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን እንዲሁም ኢትዮጵያ መድን ባህር ዳር ከተማን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
በፕሪሚየር ሊጉ ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ 
Jan 19, 2025 49
አዲስ አበባ፤ጥር 11/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር የሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ወላይታ ድቻ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ወላይታ ድቻ በሊጉ ካደረጋቸው ያለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። ሶስት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። በአምስቱ ጨዋታዎች አምስት ጎሎችን ሲያስቆጥር ስድስት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ19 ነጥብ 8ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። ሲዳማ ቡና በ18 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በሌላኛው የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። መቀሌ 70 እንደርታ በሊጉ ካደረጋቸው ያለፉት አምስት ጨዋታዎች መካከል አንዱን በድል ሲወጣ በተመሳሳይ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪዎቹ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ አንድ ግብ ሲያስቆጥር በተመሳሳይ አንድ ግብ አስተናግዷል። ቡድኑ በ15 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ ባለፉት አምስት ተከታታይ የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ ሶስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አራት ጎሎችን አስተናግዷል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ15 ነጥብ ተጋጣሚውን በግብ ክፍያ በልጦ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በተያያዘ ዜና ትናንት በተደረጉ የ15ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ቅዱስ ጊዮርጊስ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 እንዲሁም አርባምንጭ ከተማ ስሑል ሽሬን 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ ያደረገበትን ድል አስመዘገበ 
Jan 18, 2025 60
አዲስ አበባ፤ ጥር 10/2017(ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አጥቂው ፍጹም ጥላሁን በፍጹም ቅጣት ምት እና የድሬዳዋ ከተማው ተከላካይ ኢስማኤል አብዱልጋኒዩ በራሱ ግብ ላይ የማሸነፊያ ጎሎችን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ24 ነጥብ ደረጃውን ከ5ኛ ወደ 2ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱን ሰባተኛ ድሉን አስመዝግቧል። ቅዱስ ጊዮርጊስ የዛሬውን ጨምሮ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊጉ ጨዋታዎች ድል ቀንቶታል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ19 ነጥብ 6ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ድሬዳዋ የዛሬውን ጨምሮ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። በ15ኛ ሳምንት ሁለተኛ ጨዋታ ስሑልሽሬ ከአርባምንጭ ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የፕሪሚየር ሊጉ የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል
Jan 18, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ጥር 10/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። የሳምንቱ የመጀመሪያ ጨዋታ በድሬዳዋ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ መካከል ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይደረጋል። ድሬዳዋ በሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት ተከታታይ አምስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ አራት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ አራት ግቦችን ሲያስቆጥር ሁለት ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ19 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ቅዱስ ጊዮርጊስ ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ ነጥብ ተጋርቷል። በአምስቱ ጨዋታዎች ስምንት ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ስድስት ግቦችን አስተናግዷል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በ21 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። የ15ኛ ሳምንት ሁለተኛ ጨዋታ ስሑል ሽሬ እና አርባምንጭ ከተማን ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ያገናኛል። ስሑል ሽሬ በሊጉ ካደረጋቸው ያለፉት አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። በሶስቱ ሲሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ሶስት ግቦችን ሲያስቆጥር ስድስት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ11 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። አርባምንጭ ከተማ ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በአምስቱ ጨዋታዎች አራት ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ ስድስት ጎሎችን አስተናግዶ በ16 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የሊጉ መርሃ ግብር ነገም ቀጥሎ ይካሄዳል። ወላይታ ድቻ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከመቀሌ 70 እንደርታ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። አዳማ ከተማ እና ኢትዮጵያ ቡና የ15ኛ ሳምንት አራፊ ቡድኖች ናቸው። የ15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ጥር 13 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል። መቻል በ25 ነጥብ ሊጉን እየመራ ሲሆን ኢትዮጵያ መድን እና ሀዲያ ሆሳዕና በተመሳሳይ 23 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። የድሬዳዋ ከተማው መሐመድ ኑር ናስር፣ የኢትዮጵያ ቡናው አንተነህ ተፈራ እና የመቻሉ ሽመልስ በቀለ በተመሳሳይ ስድስት ግቦች የሊጉን ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት በጋራ እየመሩ ነው። የአዳማ ከተማዎቹ ነቢል ኑሪ እና ስንታየሁ መንግስቱ፣ የቅዱስ ጊዮርጊሶቹ ፍጹም ጥላሁንና አማኑኤል ኤርቦ፣ የመቀሌ 70 እንደርታው ያሬድ ብርሃኑ፣ የወላይታ ድቻው ያሬድ ዳርዛ፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ አዲስ ግደይ እና ዩጋንዳዊው ቻርልስ ሙሲጌ በተመሳሳይ አምስት ግቦች ይከተላሉ።
አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው ተሾሙ
Jan 17, 2025 73
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድን የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ አድርጎ ሾሟል። አሰልጣኝ ዮሴፍ ገብረወልድ ከዚህ ቀደም የሃዋሳ ከተማ ሴቶች ቡድን እንዲሁም ያለፉትን ሶስት ዓመታት የአርባምንጭ ከተማ ሴቶች ቡድን ዋና አሰልጣኝ በመሆን ሲሰሩ መቆያታቸውን ገልጿል። ባለፈው ዓመት በጋና አክራ የአፍሪካ ጨዋታዎች ላይም የኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድንን ማሰልጠናቸውን አስታውሷል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ትናንት ባደረገው ስብሰባ አሰልጣኝ ዮሴፍ የብሔራዊ ቡድኑን ኃላፊነት እንዲረከቡ ውሳኔ አሳልፏል። አሰልጣኙም የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድንን ለመጪዎቹ ሁለት ዓመታት ለማሰልጠን እንዲሁም የአርባምንጭ ከተማ ኃላፊነታቸውን በመልቀቅ ሙሉ ለሙሉ ትኩረታቸውን ብሔራዊ ቡድኑ ላይ ለማድረግ ተስማምተዋል። አሰልጣኝ ዮሴፍ ከአንድ ወር በኋላ በ2026 የሴቶች አፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የመጀመርያ ዙር ዩጋንዳን የሚገጥመውን ቡድን በማዘጋጀት የብሔራዊ ቡድን ሥራቸውን እንደሚጀምሩ የፌዴሬሽኑ መረጃ ያመለክታል።
ባህላዊ ስፖርቶች የአብሮነትና የህብረ ብሄራዊነት መገለጫ ናቸው
Jan 16, 2025 76
አዲስ አበባ፤ጥር 8/2017(ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ ከተማ "የባህል ስፖርቶች ለህብረ ብሄራዊ አንድነት"በሚል መሪ ሃሳብ ከታህሳስ 26 ቀን 2017 ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው 15ኛው ከተማ አቀፍ የባህል ስፖርት ውድድር እና ፌስቲቫል ተጠናቋል። በውድድሩ አስራ አንዱ ክፍለ ከተሞች በዘጠኝ የስፖርት ዓይነቶች የተሳተፉ ሲሆኑ በሁሉቱም ጾታዎች ከ10 ሺህ በላይ ስፖርተኞች ተሳታፊ ሆነዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ በላይ ደጀን ፤ባህላዊ ስፖርት ለዛሬው ዘመናዊ ስፖርት መሰረት መሆኑን ነው የገለጹት። ባህላዊ ስፖርትን በህብረተሰቡ ዘንድ ለማጎልበትና ለማስረፅ በ10 ዓመቱ የልማት ዕቅድ ውስጥ በማካተት ከትምህርት ቤት ጀምሮ ተግባራዊ እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። አሰራሩ ተማሪዎች ከልጅነታቸው አንስቶ ከቀለም ትምህርት ጎን ለጎን ባህላዊ ትውፊታቸውን እንዲያውቁ የሚያግዝ ነው ብለዋል። ባህላዊ ስፖርት የአብሮነትና የህብረ ብሄራዊነት መገለጫ በመሆኑ ከመቼውም ጊዜ በላይ ትኩረት ሰጥተን ልንሰራበት ይገባል ብለዋል። መርኃ ግብሩ በ22ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ፌስቲቫል ላይ አዲስ አበባን ወክለው የሚሳተፉ ስፖርተኞች የተመረጡበት መሆኑን አመላክተዋል ። ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች 8 ወርቅ ፣ 10 ብር እና 4 ነሃስ በድምሩ 56 ሜዳሊያ በማስመዝገብ ውድድሩን በበላይነት ሲያጠናቅቅ አቃቂ ቃሊቲ ሁለተኛ፣ቦሌ ክፍለ ከተማ ሶስተኛ ሆነዋል። በቡብ፣በፈረስ ጉግስ ፣በፈረሰ ሽርጥ ፣በኩርቦ፣በሻህ ፣በቀስት፣በገበጣ ፣በገና ፣ በትግል በሁሉቱም ፆታ ማካሄድ መቻሉም ተገልጿል ። የዘንድሮውን ውድድር ያዘጋጀው ቦሌ ክፍለ ከተማ ሲሆን ቀጣዩን ውድድር ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ እንዲያዘጋጅ ተመርጧል።
የሊጉ የ14ኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ 
Jan 16, 2025 87
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2016 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት መርሃ ግብር የመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። የዕለቱ የመጀመሪያ መርሃ ግብር ፋሲል ከነማ እና ኢትዮጵያ ቡናን ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ያገናኛል። ፋሲል ከነማ ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች በሁለቱ ድል ሲቀናው ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ አራት ግቦችን ሲያስቆጥር ሁለት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ16 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው ያለፉት አምስት ጨዋታዎች ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። ሁለት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ አራት ጎሎችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ ሁለት ግቦችን አስተናግዷል። ኢትዮጵያ ቡና በ16 ነጥብ ተጋጣሚውን በግብ ክፍያ በልጦ 9ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ14ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ መድን ከሃዋሳ ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ መድን ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አላስተናገደም። ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ስምንት ጎሎችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ኢትዮጵያ መድን በ20 ነጥብ 5ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሃዋሳ ከተማ በበኩሉ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ አንድ ግብ ብቻ ሲያስቆጥር ሶስት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሃዋሳ ከተማ በ10 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በተያያዘ ዜና ትናንት በተደረጉ የ14ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች ወላይታ ድቻ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን 2 ለ 0 ሲረታ ሲዳማ ቡና እና መቀሌ 70 እንደርታ ያደረጉት ጨዋታ ያለ ምንም ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል።
ወላይታ ድቻ ወደ አሸናፊነት የተመለሰበትን ድል አስመዝግቧል
Jan 15, 2025 60
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2016 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ወላይታ ድቻ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን 2 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ያሬድ ዳርዛ በ8ኛው ደቂቃ እና ተቀይሮ የገባው ብስራት በቀለ በ84ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ወላይታ ድቻ ከአምስት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል። በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ድሉን ያገኘው ወላይታ ድቻ በ19 ነጥብ ደረጃውን ከ10ኛ ወደ 7ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በሊጉ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን 18ኛ ደረጃ ይዟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በሊጉ እስከ አሁንም ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛው ክለብ ነው። በተያያዘም ቀን ላይ በተደረገ የ14ኛ ሳምንት ጨዋታ ሲዳማ ቡና እና መቀሌ 70 እንደርታ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል።
በፕሪሚየር ሊጉ ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ
Jan 15, 2025 84
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2017(ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት መርሃ ግብር የሶስተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ሲዳማ ቡና ከመቀሌ 70 እንደርታ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሲዳማ ቡና በሊጉ ካደረጋቸው ያለፉት አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሶስት ጊዜ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ስምንት ግቦችን አስተናግዷል። ሲዳማ ቡና በ17 ነጥብ 7ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። ሶስት ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። በአምስቱ ጨዋታዎች ሁለት ጎሎችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ በተመሳሳይ ሁለት ግቦች ተቆጥረውበታል። መቀሌ 70 እንደርታ በ14 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በሌላኛው የ14ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከወላይታ ድቻ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በሊጉ ካደረጋቸው ያለፉት አምስት ጨዋታዎች በአራቱ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ምንም ጎል ማስቆጠር አልቻለም። በአንጻሩ ሰባት ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን 18ኛ ደረጃን ይዟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ድል ያላስመዘገበ ብቸኛው ክለብ ነው። ወላይታ ድቻ በበኩሉ ባለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። አንድ ጊዜ ሲሸነፍ አራት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ስድስት ጎሎችን አስተናግዷል። ወላይታ ድቻ በ16 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በተያያዘ ዜና ትናንት በተደረጉ የ14ኛ ሳምንት የሁለተኛ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 1 ለ 0 ሲያሸንፍ የሊጉ መሪ መቻል እና ድሬዳዋ ከተማ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም