ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ተጠባቂ ጨዋታ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን አሸነፈ
Dec 14, 2025 66
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ማህሌት ምትኩ በ35ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። በጨዋታው ላይ ድንቅ ብቃቷን ያሳየችው ማህሌት ምትኩ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በውድድር ዓመቱ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ነጥቡን ወደ 33 ከፍ አድርጓል። በሊጉ የመጀመሪያ ሽንፈቱን ያስተናገደው የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታዎች እየቀሩት በ25 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረገ ሌላኛው ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ እና አዳማ ከተማ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ13ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከታህሳስ 8 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ እንደሚካሄዱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
በሊጉ ተጠባቂ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ክሪስታል ፓላስን አሸንፏል
Dec 14, 2025 62
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ ክሪስታል ፓላስን 3 ለ 0 አሸንፏል። በስልኸረስት ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሊንግ ሃላንድ በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ፊል ፎደን ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የጨዋታው ኮከብ ሆኖ የተመረጠው ሃላንድ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ግቦች ወደ 17 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን አጠናክሯል። በሊጉ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ ነጥቡን ወደ 34 ከፍ በማድረግ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ አራተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ክሪስታል ፓላስ በ26 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች አስቶንቪላ ዌስትሃም ዩናይትድን 3 ለ 2 በማሸነፍ በ33 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ኖቲንግሃም ፎረስት ቶተንሃም ሆትስፐርስን 3 ለ 0፣ ሰንደርላንድ ኒውካስትል ዩናይትድን 1 ለ ዐ አሸንፈዋል። ብሬንትፎርድ እና ሊድስ ዩናይትድ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። የ16ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር በማንችስተር ዩናይትድ እና ቦርንማውዝ መካከል ነገ ይደረጋል።
ሲዳማ ቡና እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ለኢትዮጵያ ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ አለፉ
Dec 14, 2025 57
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሶስተኛ ዙር የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገዋል። በአዳስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሲዳማ ቡና አርባምንጭ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ፍቅረየሱስ ተክለብርሃን እና ብሌዝ ናጎ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ንብ እግር ኳስ ክለብን 2 ለ 1 አሸንፏል። ያሬድ ከበደ በጨዋታ እና ጌትነት ተስፋዬ በቀለም ቅጣት ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ኢዮብ ደረሰ ለንብ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ውጤቶቹን ተከትሎ ሲዳማ ቡና እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ለሩብ ፍጻሜ አልፈዋል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ ቤንች ማጂ ቡና ደብረብርሃን ከተማን በመለያ ምት አሸንፎ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅለዋል። ኢትዮጵያ መድን፣ መቻል፣ ነጌሌ አርሲ እና ቦዲቲ ከተማ ሌሎች ለሩብ ፍጻሜ ያለፉ ክለቦች ናቸው። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር የመጨረሻ መርሃ ግብር ነገ በኢትዮጵያ ቡና እና መቀሌ 70 እንደርታ መካከል በአዲስ አበባ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ይደረጋል።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ቤንች ማጂ ቡና ለሩብ ፍጻሜ አለፈ
Dec 14, 2025 75
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር ቤንች ማጂ ቡና ደብረብርሃን ከተማን በመለያ ምት አሸንፏል። በአዳስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቡድኖቹ በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሀይደር ሽኩር ለደብረብርሃን ከተማ፣ መሐመድ ናስር ለቤንች ማጂ ቡና ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቶ ቤንች ማጂ ቡና 5 ለ 4 አሸንፏል። ቤንች ማጂ ቡና ለሩብ ፍጻሜ ያለፈ አምስተኛ ቡድን ሆኗል። በአሁኑ ሰዓት ሲዳማ ቡና ከአርባ ምንጭ ከተማ በአዲስ አበባ ስታዲየም እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከንብ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ድሬዳዋ ከተማ እና አዳማ ከተማ አቻ ተለያዩ
Dec 14, 2025 59
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ድሬዳዋ ከተማ እና አዳማ ከተማ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዝናሽ ሰለሞን እና ዘለቃሽ አሰፋ በመጀመሪያ አጋማሽ ባስቆጠሯቸው ግቦች አዳማ ከተማ መሪ ሆኗል። ከእረፍት መልስ ሲፋን ተስፋዬ በጨዋታ እና ምስር ኢብራሂም በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ ባሰረፏቸው ግቦች አዳማ ከተማ አቻ ሆኗል። አዳማ ከተማ በ15 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ በ13 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ከቀኑ 9 ሰዓት የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
የኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታ
Dec 14, 2025 64
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ ካደረጋቸው 11 ጨዋታዎች መካከል በ10ሩ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። 29 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ30 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባካሄዳቸው ዘጠኝ ጨዋታዎች ስምንቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይቷል። 27 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ የተቆጠረበት አንድ ግብ ብቻ ነው። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ25 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሊጉ በርካታ ግቦችን ያስቆጠረ ቡድን ሲሆን ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በበኩሉ በሊጉ ዝቅተኛ የግብ መጠን ያስተናገደ ቡድን ነው። በሊጉ አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኙት ክለቦች ጨዋታ በዋንጫ ፉክክሩ ላይ ተጽእኖ ይኖረዋል። በሌላኛው መርሃ ግብር ድሬዳዋ ከተማ ከአዳማ ከተማ ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይጫወታሉ። ድሬዳዋ ከተማ በ12 ነጥብ ዘጠነኛ፣ አዳማ ከተማ በ14 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ለሩብ ፍጻሜ የሚያልፉ ክለቦች የሚለዩባቸው ጨዋታዎች ዛሬም ቀጥለው ይካሄዳሉ
Dec 14, 2025 65
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር የሁለተኛ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየም ደብረብርሃን ከተማ ከቤንች ማጂ ቡና ከቀኑ 7 ሰዓት እና ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ። ሲዳማ ቡና አምና የኢትዮጵያ ዋንጫ የፍጻሜ ተፋላሚ እንደደነበር የሚታወስ ነው። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከንብ እግር ኳስ ክለብ ከቀኑ 7 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ትናንት በተደረጉ የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ነጌሌ አርሲ፣ ቦዲቲ ከተማ፣ ኢትዮጵያ መድን እና መቻል ለሩብ ፍጻሜ አልፈዋል።
በፕሪሚየር ሊጉ ክሪስታል ፓላስ ከማንችስተር ሲቲ ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Dec 14, 2025 59
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 5/2018 (ኢዜአ):- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት ሁለተኛ ቀን ውሎ አምስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 11 ሰዓት ክሪስታል ፓላስ ከማንችስተር ሲቲ በሰልኸረስት ፓርክ ስታዲየም ይጫወታሉ። ክሪስታል ፓላስ በ26 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ በ31 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች በፕሪሚየር ሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ31ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 30 ጨዋታዎች ማንችስተር ሲቲ 19 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ክሪስታል ፓላስ አራት ጊዜ ሲያሸንፍ ሰባት ጊዜ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። ማንችስተር ሲቲ በ30ዎቹ ጨዋታዎች 63 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ክሪስታል ፓላስ 30 ግቦችን አስቆጥሯል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች በነበራቸው ግንኙነት ማንችስተር ሲቲ ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥተዋል። በኦስትሪዊው ኦሊቨር ግላስነር የሚመራው ክሪስታል ፓላስ ጥሩ የውድድር ጊዜ በማሳለፍ ይገኛል። የፔፕ ጋርዲዮላው ማንችስተር ሲቲ ባለፈው ዓመት ከነበረው መጥፎ የውድድር ዓመት በኋላ ዘንድሮ ጠንካራ ግስጋሴ እያደረገ ነው። በፕሪሚየር ሊጉ ከምርጥ አራቱ ሁለቱ የሆኑት ክለቦች የሚያደርጉት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። ማንችስተር ሲቲ ካሸነፈ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሁለት ዝቅ ያደርጋል። የ39 ዓመቱ ዳረን ኢንግላንድ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ሰንደርላንድ ከኒውካስትል ዩናይትድ፣ ኖቲንግሃም ፎረስት ከቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ዌስትሃም ዩናይትድ ከአስቶንቪላ በተመሳሳይ ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ብሬንትፎርድ ከሊድስ ዩናይትድ ምሽት 1 ሰዓት ከ30 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የሊጉ መሪ አርሰናል ዎልቭስን በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Dec 14, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርሰናል ዎልቭስን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በኤምሬትስ ስታዲ በተካሄደው ጨዋታ በ70ኛው ደቂቃ ቡካዮ ሳካ ከማዕዘን ምት ያሻገረውን የዎልቭሱ ግብ ጠባቂ ሳም ጆንስተን በ70ኛው ደቂቃ በራሱ ላይ አስቆጥሮ አርሰናል መሪ ሆኗል። ቶሉ አርኮዳሬ በ90ኛው ደቂቃ ዎልቭስን አቻ አድርጓል። ጨዋታው በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ ሲባል ከ11 ወራት በኋላ ከጉዳት የተመለሰው ጋብርኤል ጄሱስ በ94ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ለአርሰናል ወሳኝ ድል አስገኝቷል። በጨዋታው አርሰናል ብልጫ ወስዶ ቢጫወትም በዎልቭስ የጥልቀት መከላከል የጨዋታ ስልት ፈተና አጋጥሞታል። በውድድር ዓመቱ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው የሊጉ መሪ አርሰናል ነጥቡን ወደ 36 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ ብሏል። በአንጻሩ በሊጉ 14ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ዎልቭስ በሁለት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ እስከ አሁን በሊጉ ምንም ጨዋታ አላሸነፈም። በሊጉ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ማንችስተር ሲቲ ነገ ከክሪስታል ፓላስ ጋር ከሜዳው ውጪ የሚያደርገው ጨዋታ ይጠበቃል።
በ4ኛው የአፍሪካ ወጣቶች ኦሎምፒክ ዛሬ በተደረጉ ውድድሮች ኢትዮጵያ ተጨማሪ 3 የወርቅ ሜዳልያ አሸንፋለች
Dec 13, 2025 137
አዲስ አበባ፤ታህሳሰ 4 /2018(ኢዜአ)፦በ4ኛው የአፍሪካ ወጣቶች ኦሎምፒክ ዛሬ በተደረጉ ውድድሮች ኢትዮጵያ ተጨማሪ 3 የወርቅ ሜዳልያ አሸንፋለች። 4ኛው የአፍሪካ ወጣቶች ኦሎምፒክ ጨዋታ ውድድር እየተካሄደ ነው:: ዛሬ በተደረጉ ውድድሮችም ኢትዮጵያ ተጨማሪ 3 የወርቅ ሜዳልያ አሸንፋለች። በ1500 ሜትር ሴቶች ሀና ረጋሳ ውድድሯን በአንደኛነት በመፈፀም ለኢትዮጵያ የወርቅ ሜዳልያ አሸንፋለች። በተጨማሪም በ800ሜትር ሴቶች መርጋ ሀቃ የወርቅ ሜዳልያ አሸንፏል። ኢትዮጵያ በ5ሺ ሜትር እርምጃ ውድድር በህይወት አምባው አማካኝነት የውድድሩን 6ኛ የወርቅ ሜዳልያ አሸንፋለች። በ3000ሺ ሜትር ወንዶች ጎይቶም መኮንን የነሀስ ሜዳልያ አሸንፏል።በመካከለኛ ሪሌይ የነሐስ ማዳልያ ተመዝግቧል። እንደ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ ከ2ኛው የኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ወጣቶች ጨዋታዎች የተገኙ አትሌቶች በውድድሩ በአስገራሚ ውጤታማነታቸው ቀጥለዋል። #ኢዜአ #Ethiopian_News_Agency
በፕሪሚየር ሊጉ ቼልሲ እና ሊቨርፑል ድል ቀንቷቸዋል
Dec 13, 2025 123
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬ መካሄድ ጀምረዋል። በስታምፎርድ ብሪጅ በተካሄደው ጨዋታ ቼልሲ ኤቨርተንን 2 ለ 0 አሸንፏል። ከጉዳት የተመለሰው ኮል ፓልመር እና ማሎ ጉስቶ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቼልሲ በ28 ነጥብ ደረጃውን ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። ኤቨርተን በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው ጨዋታ ሊቨርፑል ብራይተንን 2 ለ 0 አሸንፏል። ሁጎ ኢኪቲኬ የማሸነፊያ ግቦችን አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል በ26 ነጥብ ስድስተኛ፣ ብራይተን በ23 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። የሊቨርፑል አጥቂ ሁጎ ኢኬቲኬ በ47ኛው ሴኮንድ ያስቆጠራት ጎል የውድድር ዓመቱ ፈጣን ጎል ተመዝግቧል። ምሽት 5 ሰዓት ላይ የሊጉ መሪ አርሰናል ከዎልቭስ በኤምሬትስ ስታዲየም ጨዋታውን ያደርጋል። ከዚያ አስቀድሞ በርንሌይ ከፉልሃም ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ኢትዮጵያ መድን እና መቻል ለሩብ ፍጻሜ አለፉ
Dec 13, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተከናውነዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን ቢሾፍቱ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። አማኑኤል ኤርቦ እና ዩጋንዳዊው አለን ካይዋ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ መቻል ድሬዳዋ ከተማን በመለያ ምት አሸንፏል። ጨዋታው በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አንድ አቻ አጠናቋል። ዮዳሄ ዳዊት ለመቻል እና ጃፋር ሙደሲር ለድሬዳዋ ከተማ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። መቻል በመለያ ምት 5 ለ 4 ማሸነፍ ችሏል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ መድን እና መቻል ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅለዋል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ነጌሌ አርሲ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማን፣ ቦዲቲ ከተማ ባህር ዳር ከተማን በማሸነፍ ለሩብ ፍጻሜ አልፈዋል። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር ጨዋታዎች ነገ እና ከነገ በስቲያ ይደረጋሉ።
ጤናማ እና አምራች ዜጋን በማፍራት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ስፖርታዊ እንቅስቃሴን ልማድ ማድረግ ይገባል
Dec 13, 2025 91
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ ጤናማ እና አምራች የሰው ሀይልን በማፍራት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ስፖርታዊ እንቅስቃሴን ልማድ ማድረግ እንደሚገባ ተመላከተ። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን በቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ያስገነባውን የስፖርት ማዘወተሪያ ስፍራ አስመርቋል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሰሃ ይታገሱ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደተናገሩት፤ ስፖርት የሰዎችን ማህበራዊ መስተጋብር በማጠናከር አብሮ የመስራት ባህልን የሚያጎለብት ነው። ኢንዱስትሪዎች የተለያዩ ምርቶችን ለማምረት የሚሰሯቸውን ስራዎች ውጤታማ ለማድረግ አምራች የሰው ሀይል የጀርባ አጥንት ነው ብለዋል። በመሆኑም የሰው ሀይላቸውን በአግባቡ ለመጠቀም፣ ውጤታማ ለማድረግና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ጤንነቱ የተጠበቀ አምራች ዜጋ መገንባት ግድ መሆኑን አስገንዝበዋል። በቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን የተገነባው የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራም የኢኮኖሚ ዞኑ ሰራተኞች እና የአካባቢው ማህበረሰብ የሚገለገልበት መሆኑን አስታውቀዋል። የቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ዋና ሥራ አስኪያጅ ቶሎሳ በዳዳ በበኩላቸው፤ የስፖርት ማዘወትሪያ ስፍራዎቹ ሰራተኞቹ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ጤንነታቸውን እንዲጠብቁ የሚያደርጉ ናቸው ብለዋል። የስፖርት ማዘወተሪያ ስፍራው የእግር ኳስና የቅርጫት ኳስ ጨምሮ ሌሎች የስፖርት ዓይነቶችን ማከናወን የሚያስችሉ ስፍራዎችን ማካተታቸውን ጠቅሰዋል። የአዲስ አበባ የቅርጫት ኳስ ፌዴሬሽን ጽህፈት ቤት ኃላፊ አለምነህ ስዩም እንደ ሀገር ጤናማ ማህበረሰብ ለመፍጠር የስፖርት ማዘወተሪያ ስፍራ መስፋፋት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ቦዲቲ ከተማ ባህር ዳር ከተማን በማሸነፍ ለሩብ ፍጻሜ አለፈ
Dec 13, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር ቦዲቲ ከተማ ባህር ዳር ከተማን በመለያ ምት አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሳምሶን ቆልቻ በ21ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠራት ግብ ቦዲቲ ከተማን መሪ አድርጋለች። አናንያ ጌታቸው በ35ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፋት ጎል ባህር ዳር ከተማ አቻ ሆኗል። ጨዋታው በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት በመጠናቀቁ ወደ መለያ ምት ያመራ ሲሆን ቦዲቲ ከተማ 6 ለ 5 አሸንፏል። ውጤቱንም ተከትሎ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የሚወዳደረው ቦዲቲ ከተማ ነጌሌ አርሲን ተከትሎ ለሩብ ፍጻሜ ያለፈ ሁለተኛ ቡድን ሆኗል። በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያ መድን ከቢሾፍቱ ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም፣ መቻል ከድሬዳዋ ከተማ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ መቻል አዲስ አበባ ከተማን በማሸነፍ ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Dec 13, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት መቻል አዲስ አበባ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተደረገው መዲና አወል እና ቤዛዊት ንጉሴ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሊጉ ስምንተኛ ድሉን ያስመዘገበው መቻል በ26 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዲስ አበባ ከተማ በአምስት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረገ የ12ኛ ሳምንት ጨዋታ ቦሌ ክፍለ ከተማ እና ሃዋሳ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
ነጌሌ አርሲ በኢትዮጵያ ዋንጫ ለሩብ ፍጻሜ ያለፈ የመጀመሪያው ክለብ ሆኗል
Dec 13, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር ዛሬ ተጀምሯል። ረፋድ ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው የመጀመሪያ ጨዋታ ነጌሌ አርሲ አቃቂ ክፍለ ከተማን 4 ለ 0 አሸንፏል። ርሆቦት ሰላሎ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አለኝታ ማርቆስ እና ሀቢብ ከማል ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ነጌሌ አርሲ በኢትዮጵያ ዋንጫ ለሩብ ፍጻሜ ያለፈ የመጀመሪያው ክለብ ሆኗል። የኢትዮጵያ ዋንጫ የመጀመሪያ ቀን ቀሪ ጨዋታዎች ከቀትር በኋላ ይካሄዳሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ቦሌ ክፍለ ከተማ እና ሃዋሳ ከተማ ነጥብ ተጋርተዋል
Dec 13, 2025 62
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ቦሌ ክፍለ ከተማ እና ሃዋሳ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ጨዋታው ረፋድ ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ተካሄዷል። ሃዋሳ ከተማ በ26 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ20 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ከቀኑ 7 ሰዓት አዲስ አበባ ከተማ ከመቻል በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ብሄራዊ ምልክት የሆነው አንጋፋው የኢትዮጵያ ዋንጫ ውድድር
Dec 13, 2025 65
የኢትዮጵያ ዋንጫ በ1937 ዓ.ም የተጀመረ አንጋፋ የጥሎ ማለፍ ውድድር ነው። ውድድሩ በወቅቱ የነበረውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር (አሁን የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ) ለመደገፍ ነበር። የጥሎ ማለፍ ውድድር ፎርማት የሆነው የኢትዮጵያ ዋንጫ እንደ እንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ እና በሌሎች ሀገራት ከሚደረጉ ውድድሮች ተመሳሳይነት ያለው ነው። በውድድሩ የመጀመሪያ ዓመታት ላይ ይሳተፉ የነበሩ ክለቦች በአዲስ አበባ እና ዙሪያ የሚገኙ ክለቦች ናቸው። የእግር ኳስ መዋቅሮችን ለመዘርጋት እና ሀገር በቀል አቅምን ለመለየት የመጀመሪያ ዓመታት ውድድሮች ወሳኝ ሚና ነበራቸው። በኢትዮጵያ አቆጣጠር 1950ዎቹ እና 1960ዎቹ ላይ የኢትዮጵያ ዋንጫ በጊዜ ሂደት እየሰፋ በመምጣት ብሄራዊ እውቅናን ያገኘ ሲሆን በተለያዩ የሀገሪቷ ክፍሎች የሚገኙ ክለቦች በስፋት መሳተፍ ጀመሩ። ውድድሩ የብሄራዊ አንድነት መገለጫ እና መሳሪያ መሆንም ችሏል። የእግር ኳስ መሰረተ ልማት እያደገ መምጣት በተለይም የስታዲየሞች እና የልምምድ ስፍራዎች መስፋት የሊግ ውድድሮች ለኢትዮጵያ ዋንጫ እድገት የበኩላቸውን ሚና ተጫውተዋል። በታህሳስ ወር 1928 ዓ.ም የተመሰረተው የመጀመሪያው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ክለብ ቅዱስ ጊዮርጊስ ውድድሩን ለበርካታ ጊዜያት በማንሳት የበላይነቱን ይዟል። ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1970ዎች እና በ1980 ዎቹ የመንግስት እና የንግድ ድርጅቶች መሳተፍ የጀመሩበት ወቅት ነው። ኢትዮጵያ ቡና፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ (በድሮ አጠራሩ መብራት ሃይል)፣ እርሻ ሰብል፣ ኢትዮ ሲሚንቶ፣ መቻል እና ኢትዮጵያ መድን ከተሳታፊዎቹ መካከል ይጠቀሳሉ። 1970ዎች እና በ1980ዎቹ የኢትዮጵያ ዋንጫ ውድድር የበለጠ ቅርጽ እየያዘ እና እየተዋቀረ የመጣበት ወቅት ነው። የመርሃ ግብሮች የጊዜ ሰሌዳ፣ ሽልማት ክፍፍል እና የዳኝነት አሰራሩ መሻሻል ያሳየበት ነው። የመገናኛ ብዙሃን የዘገባ ሽፋን መስፋትም ውድድሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ ቁልፍ ስፖርታዊ ሁነት እንዲሆን አስችሎታል። በኢትዮጵያ በ1980ዎቹ መጀመሪያ ላይ የኢትዮጵያ ዋንጫ ከካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ (ካፍ) ውድድሮች ጋር በማስተሳሰር ክለቦች በአህጉር አቀፍ ደረጃ የመሳተፍ እድል እንዲያገኙ አስችሏል። በ199ዎቹ እና በኢትዮጵያ ሚሊኒየም ከሁለት ሺህ በኋላ የኢትዮጵያ ዋንጫ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የስፖርት አፍቃሪ በስታዲየም ገብቶ የሚመለከተው እና ሰፊ የሚዲያ ሽፋን ያገኘ ሆኗል። የኢትዮጵያ ዋንጫ የሚያሸንፉ ቡድኖች የካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ተሳታፊ በመሆን ይሳተፋሉ። የኢትዮጵያ ዋንጫ በተለያዩ ምክንያቶች በተለያዩ ጊዜያት ተቋርጦ የነበረ ቢሆንም አሁንም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ምልክት ሆኖ ቀጥሏል። ውድድሩ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ባህል እና እድገት መለኪያ መሆን የቻለ ሲሆን በዜጎች መካከል የእርስ በእርስ ትብብርን በመፍጠር ረገድ የበኩሉን ሚና ተወጥቷል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ሲነሳ የኢትዮጵያ ዋንጫን አለማንሳት አይቻልም። መቻል እና ቅዱስ ጊዮርጊስ የኢትዮጵያን ዋንጫ በብዛት ማንሳት ስኬታማው ክለብ ናቸው። ኢትዮ ኤሌክትሪክ፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ፣ እርሻ ሰብል፣ አዳማ ከተማ፣ ኢትዮጵያ ቡና፣ ሲዳማ ቡና፣ ሃዋሳ ከተማ እና ወላይታ ድቻ ሌሎች የኢትዮጵያ ዋንጫን ካነሱ ክለቦች መካከል ይጠቀሳሉ። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር ከታህሳስ 4 እስከ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ቅዳሜ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ከነጌሌ አርሲ ከረፋዱ አራት ሰዓት፣ ባህር ዳር ከተማ ከቦዲቲ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት እና ኢትዮጵያ መድን ከቢሾፍቱ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። በአዲስ አበባ ስታዲየም መቻል ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። መርሃ ግብሩ እሁድም ቀጥሎ ሲውል ደብረ ብርሃን ከተማ ከቤንች ማጂ ቡና በአዲስ አበባ ስታዲየም እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከንብ እግር ኳስ ክለብ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተመሳሳይ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና ከአርባ ምንጭ ከተማ በአዲስ አበባ አበባ ስታዲየም ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ ። ሰኞ ታህሳስ 6 ቀን 2018 ዓ.ም ኢትዮጵያ ቡና ከመቀሌ 70 እንደርታ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በሶስተኛው ዙር የሚያሸንፉ ክለቦች ለሩብ ፍጻሜ ያልፋሉ። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ በአንደኛው ዙር መሰናበቱ የሚታወስ ነው። የኢትዮጵያ ዋንጫን የሚያሸንፈው ቡድን በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን ወክሎ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ይሳተፋል።
የሊጉ መሪ አርሰናል ከዎልቭስ ጋር ይጫወታል
Dec 13, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ):- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 16ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። ምሽት አምስት ሰዓት ላይ አርሰናል ዎልቭስን በኤምሬትስ ስታዲየም ያስተናግዳል። አርሰናል ሊጉን በ33 ነጥብ እየመራ ሲሆን ዎልቭስ በሁለት ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። አርሰናል በውድድር ዓመቱ ባደረጋቸው 15 ጨዋታዎች በ10ሩ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፎ በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። አርሰናል ባከናወናቸው በጨዋታዎች 28 ግቦችን ሲያስቆጥር ዘጠኝ ግቦች አስተናግዷል። ተጋጣሚው ዎልቭስ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ አላሸነፈም። በ13ቱ ሲሸነፍ ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። ባከናወናቸው 15 ጨዋታዎች ስምንት ጎሎችን ሲያስቆጥር 33 ግቦች ተቆጥረውበታል። አርሰናል በ15ኛ ሳምንት በአስቶንቪላ ከደረሰበት ሽንፈት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። በፕሪሚየር ሊጉ መጥፎ የውድድር ዓመት እያሳለፈ የሚገኘው ዎልቭስ በሊጉ የመጀመሪያ ሶስት ነጥቡን ለማግኘት ከባድ ፈተና ይጠብቀዋል። አርሰናል ጨዋታውን የማሸነፍ ሰፊ ግምት ያገኘ ሲሆን ካሸነፈ ከተከታያቸው ማንችስተር ሲቲ ጋር ያላቸውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ ያደርጋሉ። የ38 ዓመቱ ሮበርት ጆንስ ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ቼልሲ ከኤቨርተን እና ሊቨርፑል ከብራይተን በተመሳሳይ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በርንሌይ ከፉልሃም ምሽት 2 ሰዓት 30 ላይ ይጫወታሉ።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ የሚደረጉ ጨዋታዎች
Dec 13, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 12ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ቦሌ ክፍለ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቦሌ ክፍለ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 11 ጨዋታዎች አምስቱን ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። አራት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 13 ግቦችን ሲያስቆጥር 11 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ19 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሃዋሳ ከተማ 11 ጨዋታዎችን አድርጎ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። 22 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ዘጠኝ ግቦች ተቆጥረውበታል። ሃዋሳ ከተማ በ25 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኖቹ በአሸናፊነት ጉዟቸው ለመቀጠል የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ11ኛ ሳምንት ጨዋታ የሊጉን መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር አዲስ አበባ ከተማ ከመቻል ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው 11 ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ስምንት ጊዜ ሲሸነፍ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። አምስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 22 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃ ይዟል። በሊጉ ካከናወናቸው 11 ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ያሸነፈው መቻል ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 18 ግቦችን በ11ዱ ጨዋታዎች ላይ ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። መቻል በ23 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ሁለተኛ ድሉን ለማስመዝገብ፣ መቻል ወደ መሪዎቹ መጠጋት የሚያስችለውን ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይጫወታሉ።