ቀጥታ፡
ስፖርት
በሴካፋ ዞን ማጣሪያ ኢትዮጵያ ደቡብ ሱዳንን አሸነፈች 
Nov 18, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 9/2018 (ኢዜአ)፦ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ የምድብ አንድ ጨዋታ አዘጋጇ ኢትዮጵያ ደቡብ ሱዳንን 4 ለ 1 አሸንፋለች። በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ዳዊት ካሳው ሶስቱን ግቦች በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ዳዊት በውድድሩ ላይ ሀትሪክ የሰራ የመጀመሪያው ተጫዋች ሆኗል። እንየው ስለሺ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል።   ፓኖም ጁዎ ለደቡብ ሱዳን ብቸኛውን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት አስቆጥሯል። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን በተጋጣሚው ላይ ከፍተኛ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ ነጥቧን ወደ ስድስት ከፍ በማድረግ የምድቡን መሪነት አጠናክሯል። ቡድኑ ቀጣይ ጨዋታውን አርብ ህዳር 12 ቀን 2018 ዓ.ም ከሶማሊያ ጋር ያደርጋል።   ደቡብ ሱዳን በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን አምስተኛ ደረጃ ይዛለች። አጥቂው ዳዊት ካሳው በውድድሩ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ አራት ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን መምራት ጀምሯል። በምድብ አንድ ሌላኛው መርሃ ግብር ሶማሊያ ከኬንያ ከቀኑ 10 ሰዓት በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ኢትዮጵያ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ሁለተኛ ጨዋታዋን ዛሬ ከደቡብ ሱዳን ጋር ታደርጋለች 
Nov 18, 2025 68
አዲስ አበባ፤ ህዳር 9/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ አዘጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ዛሬ አራተኛ ቀኑን ይዟል። በዕለቱ የምድብ ሁለተኛ ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ኢትዮጵያ ከደቡብ ሱዳን ጋር ከቀኑ 7 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ትጫወታለች። በምድብ አንድ የምትገኘው ኢትዮጵያ በመጀመሪያ ጨዋታዋ ሩዋንዳን ዳዊት ካሳ እና ሁዜፋ ሻፊ ግቦች 2 ለ 0 አሸንፋለች። ምድቡንም በሶስት ነጥብ እየመራ ይገኛል። በአሜሪካዊው ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው ታዳጊ ብሄራዊ ቡድኑ በጨዋታው ላይ ያሳየው ብቃት በብዙዎች አድናቆት አስችሮታል። ተጋጣሚዋ ደቡብ ሱዳን ከሶማሊያ ጋር ባደረገችው የመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ ሁለት አቻ መለያየቷ ይታወቃል። ኢትዮጵያ የዛሬውን ጨዋታ ካሸነፈች ወደ ግማሽ ፍጻሜ የማለፍ እድሏን ታሰፋለች። በምድብ አንድ ሌላኛው መርሃ ግብር ሶማሊያ ከኬንያ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ መታሰቢያ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሶማሊያ በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታ ከደቡብ ሱዳን ጋር ሁለት አቻ ተለያይታለች። ኬንያ በምድቧ የመጀመሪያ ጨዋታዋን ታደርጋለች። በምድብ ሁለት መርሃ ግብር ሱዳን ከዩጋንዳ በድሬዳዋ ዓለም አቀፍ ስታዲየም ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ሱዳን በመጀመሪያ ጨዋታዋ በታንዛንያ 6 ለ 0 ስትሸነፍ በአንጻሩ ዩጋንዳ ብሩንዲን 4 ለ 0 አሸንፋለች። በዚሁ ምድብ ምሽት ሁለት ሰዓት ላይ ታንዛንያ ከጅቡቲ በድሬዳዋ ዓለም አቀፍ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ታንዛንያ ሱዳንን 6 ለ 0 በመርታት የሴካፋ ማጣሪያን በድል ጀምራለች። ጅቡቲ በምድቧ የመጀመሪያ ጨዋታዋን ታደርጋለች። በሴካፋ ዞን ማጣሪያ 10 ሀገራት በሁለት ምድብ ተከፍለው ጨዋታቸውን እያከናወኑ ይገኛሉ። ማጣሪያው እስከ ህዳር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በማጣሪያው ለፍጻሜ የሚያልፉት ሁለት ሀገራት የሴካፋ ዞንን ወክለው ለአፍሪካ ዋንጫ ያልፋሉ። እ.አ.አ በ2026 በሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጇ ሞሮኮን ጨምሮ 16 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ብቁና ተፎካካሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Nov 17, 2025 85
ባሕርዳር፤ ሕዳር 8/2018(ኢዜአ)፡- በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ መድረክ የሚወክሉ ብቁና ተፎካካሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ባሕልና ስፖርት ሚኒስትር ሽዊት ሻንካ ገለጹ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና ማሕበራዊ ልማት፣ ባሕልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት የባሕር ዳር ስታዲየምን እየጎበኙ ነው። በጉብኝቱ ላይ የተገኙት የባሕልና ስፖርት ሚኒስትር ሽዊት ሻንካ እንደተናገሩት፤ ለስፖርት ዘርፍ እድገት በትኩረት እየተሰራ ነው። ይህም እግር ኳስን ጨምሮ በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ኢትዮጵያን ወክለው በዓለም አቀፍ መድረክ ብቁ ተፎካካሪ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ከእነዚህም ደረጃቸውን ጠብቀው እየተከናወኑ ያሉ ታላላቅ፣ መካከለኛና አነስተኛ ስታድየሞች ግንባታን ጠቅሰዋል።   ይህም ታዳጊና ህፃናትን መሰረት ያደረገ እንደሆነ ጠቁመው፤ ተግባሩ ይበልጥ ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ አረጋግጠዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና ማሕበራዊ ልማት፣ ባሕልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ታደለ ቡራቃ(ዶ/ር) በበኩላቸው፣ በሀገሪቱ ብቁ ስፖርተኞችን ለማፍራት ህፃናትና ታዳጊዎች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ማረጋገጥ ችለናል ብለዋል። በሁሉም አካባቢዎች እየተገነቡ የሚገኙ ስታድየሞች ደረጃቸው ከፍ ያለና የሀገሪቱን የስፖርት ዘርፍ እድገት ለማላቅ የሚያግዙ እንደሆኑም ገልጸዋል። የዛሬው ምልከታም ለተወካዮች ምክር ቤት የሚቀርቡ የዘርፉን ሪፖርቶች ትክክለኛነት ያረጋገጥንበት ነው ብለዋል። የአማራ ክልል ርዕስ መስተዳድር የሕዝብ ግንኙነት አማካሪ እርዚቅ ኢሣ ፤ የባሕርዳር ስታድየም የፊፉን እና ካፍን መስፈርቶች ማሟላት በሚችል አግባብ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   ስታዲዮሙ እግር ኳስን ጨምሮ ሌሎች 23 የስፖርት ዓይነቶችን ማስተናገድ እንዲችል ሆኖ የጥራት ደረጃውን ጠብቆ በመገንባት ላይ እንደሚገኝ አብራርተዋል። የስታድየሙ አብዛኛው ስራ እየተጠናቀቀ መሆኑንና ቀሪዎቹን ፈጥኖ ለመፈፀም ርብርብ እየተደረገ መሆኑም ተመላክቷል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የጤና ማሕበራዊ ልማት፣ ባሕልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት ከስታዲየሙ በተጨማሪ የዕደ ጥበብ ማዕከላት፤ የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቴክስታይልና ፋሽን ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት እንደሚጎበኙ ይጠበቃል፡፡
በሊጉ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ መድን የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው 
Nov 16, 2025 90
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 7/ 2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሃ ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ መድን ዛሬ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል። በአዲስ አበባ ስታዲየም የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና የወቅቱ የሊጉ ዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን የሚያደርጉት ጨዋታ የተመልካቾችን ትኩረት ስቧል።   ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ እስከ አሁን ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈትን አስተናግዷል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቡዱኑ በዘጠኝ ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ መድን በበኩሉ በውድድር ዓመቱ ባደረጋቸው ሶስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ድል ሲቀናው ሁለት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ አንድ ግብ ተቀጥሮበታል። መድን በአምስት ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።   ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። ሁለቱ ቡድኖች በ2017 ዓ.ም በሊጉ ያደረጓቸው ሁለት ጨዋታዎች በተመሳሳይ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል። የቡድኖች ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ ከግብጹ ፒራሚድስ ጋር በነበረው የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ ምክንያት የተራዘመ ነው። ኢትዮጵያ መድን በቀጣይ በሚገለጽ ቀን እና ቦታ ከሸገር ከተማ ጋር ቀሪውን ተስተካካይ ጨዋታ እንደሚያደርግ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ስድስተኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል  
Nov 16, 2025 69
አዲስ አበባ፤ ህዳር 7/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሁለት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከልደታ ክፍለ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ያደረጋቸውን ሶስት ጨዋታዎች አሸንፏል። በጨዋታዎቹ 12 ጎሎችን ሲያስቆጥር የተቆጠረበት አንድ ግብ ብቻ ነው። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ የሆነው ንግድ ባንክ በዘጠኝ ነጥብ ሁለት ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በዘጠኝ ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ልደታ ክፍለ ከተማ በውድድር ዓመቱ ካካሄዳቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ በተመሳሳይ በሁለት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።   በሌላኛው መርሃ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባህር ዳር በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው ። በሶስት ጨዋታዎች ሽንፈት ሲያስተናግድ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አምስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በሶስት ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ እስከ አሁን ባደረገው አራት ጨዋታ ማሸነፍ አልቻለም። ሶስት ጊዜ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡድኑ አምስት ግብ ሲቆጠርበት ምንም ጎል አላስቆጠረም። አርባምንጭ ከተማ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዛለች።
ኢትዮጵያ የምታዘጋጀው የሴካፋ ዞን ከ17 ዓመት በታች አፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ  ይጀመራል ዛሬ ይጀመራል   
Nov 15, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ዛሬ ይጀመራል። የአፍሪካ ዋንጫው እ.አ.አ በ2026 በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይከናወናል። በውድድሩ ላይ የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ የእግር ኳስ ማህበራት ምክር ቤት(ሴካፋ) ዞንን ወክለው የሚሳተፉ ሁለት ሀገራት የሚለዩበት የማጣሪያ ውድድር በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል። ሴካፋ የማጣሪያ ውድድሩ የምድብ ድልድል ከሁለት ሳምንት ገደማ በፊት በዩጋንዳ ይፋ ማድረጉ የሚታወስ ነው። በምድብ አንድ አዘጋጇ ኢትዮጵያ ከሶማሊያ፣ ኬንያ፣ ደቡብ ሱዳን እና ሩዋንዳ ጋር ተደልድላለች። ዩጋንዳ፣ ታንዛንያ፣ ጅቡቲ፣ ሱዳን እና ብሩንዲ በምድብ ሁለት የተደለደሉ ሀገራት ናቸው። ውድድሩ በአበበ ቢቂላ እና ድሬዳዋ ኢንተርናሽናል ስታዲየሞች ይካሄዳል።   ቡድኖቹ አዲስ አበባ ከገቡ በኋላ የእድሜ ተገቢነት (MRI) ምርመራ በማከናወን ዩጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ታንዛንያ፣ ሱዳን እና ጅቡቲ የምድብ ጨዋታቸውን ወደ ሚያደርጉበት ድሬዳዋ ያመሩ ሲሆን ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሶማሊያ እና ሩዋንዳ ደግሞ የምድብ ጨዋታቸውን አዲስ አበባ አበበ ቢቂላ ስታዲየም ላይ የሚያከናውኑ ይሆናል። ዛሬ አዘጋጇ ኢትዮጵያ ከሩዋንዳ ከቀኑ 10 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሶማሊያ ከደቡብ ሱዳን ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ የሚያደርጉት ጨዋታ የመክፈቻ መርሃ ግብር ይሆናል። በድሬዳዋ ኢንተርናሽናል ስታዲየም ታንዛንያ ከሱዳን ከቀኑ 11 ሰዓት፣ ብሩንዲ ከዩጋንዳ ከምሽቱ 2 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን የሴካፋ ዞን ከ17 ዓመት በታች አፍሪካ ዋንጫ የማጣርያ ውድድር ዝግጅቱን በአዲስ አበባ ሲያደርግ ቆይቷል። ብሄራዊ ቡድኑ የሚሰለጥነው በአሜሪካዊው ቤንጃሚን ዚመር ነው። ተጫዋቾቹ የተመለመሉት ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2026 የሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ለማስተናገድ ያቀረበችው ጥያቄ አካል የሆነው የ"Road to 2029" ፕሮጀክት የ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ካምፒንግ መሆኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የሴካፋ ዞን ማጣሪያ እስከ ህዳር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በማጣሪያው ለፍጻሜ የሚያልፉት ሁለት ሀገራት የሴካፋ ዞንን ወክለው ለአፍሪካ ዋንጫ ያልፋሉ። እ.አ.አ በ2026 በሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጇ ሞሮኮን ጨምሮ 16 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ መሪነቱን ያጠናከረበትን ድል አስመዘገበ 
Nov 14, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሃ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሃዋሳ ከተማን 3 ለ 2 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳግማዊት ሰለሞን በጨዋታ እና ፍጹም ቅጣት ምት ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር ማህሌት ምትኩ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ፀሐይነሽ ጁላ እና የምስራች ላቀው ለሃዋሳ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ማህሌት ምትኩ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ድሉን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ18 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ሃዋሳ ከተማ በ12 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን በሊጉ ከመረብ ላይ ያሳረፈቻቸውን ግቦች ወደ 11 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቷን አጠናክራለች። በአሁኑ ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ሲዳማ ቡና ከአዲስ አበባ ከተማ ጋር ጨዋታቸውን እያደረጉ ይገኛል።
የሊጉ መሪ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሃዋሳ ከተማ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል 
Nov 14, 2025 115
አዲስ አበባ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሁለት ጨዋታዎች በአበባ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ሃዋሳ ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ይጫወታሉ። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አራት ጊዜ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በጨዋታዎቹ ዘጠኝ ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ በሊጉ ያከናወናቸውን አምስት ጨዋታዎች አሸንፏል። 13 ግቦችን ሲያስቆጥር የተቆጠረበት አንድ ግብ ብቻ ነው። ቡድኑ በ15 ነጥብ ሊጉን እየመራ ይገኛል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት ጥሩ ጅማሮ ያሳዩት ሁለቱ ክለቦች በጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና ከአዲስ አበባ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሲዳማ ቡና በሊጉ ካደረጋቸው አራት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ሲዳማ ቡና አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በስድስት ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል አንዱን ሲያሸንፍ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በጨዋታዎቹ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር 11 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በሶስት ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
በኢትዮጵያ ዋንጫ ቀሪ ስምንት ክለቦች ቀጣዩን ዙር ተቀላቅለዋል 
Nov 13, 2025 109
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና አዳማ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። አቡበከር አዳሙ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። አህመድ ሁሴን ለአዳማ ከተማ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ባህር ዳር ከተማ ሸገር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አማኑኤል ገብረሚካኤል እና ግርማ ዲሳሳ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ድሬዳዋ ከተማ በሬድዋን ሸረፋ ግብ ሃዋሳ ከተማን 1 ለ 0 ረቷል።   በተመሳሳይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን በመለያ ምት 4 ለ 2 አሸንፏል። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይተዋል። በሌሎች ጨዋታዎች አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ 2 ለ 1 እና ቢሾፍቱ ከተማ ደሴ ከተማን 1 ለ 0 ሲያሸንፉ ንብ እግር ኳስ ክለብ የካ ክፍለ ከተማን ደብረብርሃን ከተማ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማን በመለያ ምት ማሸነፍ ችለዋል። ዛሬ እና ትናንት የተደረጉ ጨዋታዎችን ተከትሎ 16 ክለቦች ለሶስተኛው ዙር አልፈዋል።   ኢትዮጵያ መድን፣ ቤንች ማጂ ቡና፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ፣ አርባምንጭ ከተማ፣ ቦዲቲ ከተማ፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ መቻል፣ ነጌሌ አርሲ፣ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ፣ ድሬዳዋ ከተማ፣ ባህር ዳር ከተማ፣ ደብረብርሃን ከተማ፣ ንብ እግር ኳስ ክለብ፣ ቢሾፍቱ ከተማ፣ ኢትዮጵያ ቡና እና ሲዳማ ቡና 16ቱን የተቀላቀሉ ክለቦች ናቸው። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ወላይታ ድቻ ከውድድሩ ተሰናብቷል። የኢትዮጵያ ዋንጫ ሶስተኛ ዙር መርሃ ግብር በቀጣይ በሚገለጽ ቀን እና ቦታ ይካሄዳል።
መቻል፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ ነጌሌ አርሲ እና ቦዲቲ ከተማ በኢትዮጵያ ዋንጫ ወደ ሶስተኛ ዙር አለፉ
Nov 13, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ህዳር 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር መርሃ ግብር ጨዋታዎች ዛሬም እየተካሄዱ ነው። በሃዋሳ አርቴፊሻል ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ መቻል ምድረገነት ሽሬን 3 ለ 0 አሸንፏል። አብዱልከሪም ወርቁ በጨዋታ፣ ዮሴፍ ታረቀኝ በፍጹም ቅጣት እና የምድረገነት ሽሬው ክብሮም ብርሃነ በራሱ ላይ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በሌላኛው መርሃ ገብር ነጌሌ አርሲ ሀዲያ ሆሳዕናን በመለያት ምት 8 ለ 7 አሸንፏል። ሁለቱ ቡድኖች በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሀቢብ ከማል ለነጌሌ አርሲ፣ ብሩክ በየነ ለሀዲያ ሆሳዕና ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ ፋሲል ከነማን በአሸናፊ ሀፍቱ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል። ቦዲቲ ከተማ ሃላባ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በጅማ ስታዲየም በተደደረገው ጨዋታ አጥናፉ ቡሸና የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። መቻል፣ መቀሌ 70 እንደርታ፣ ነጌሌ አርሲ እና ቦዲቲ ከተማ 16ቱን ተቀላቅለዋል። ቀሪ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች ዛሬ ከሰዓት በኋላ ይካሄዳሉ። ትናንት በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን፣ አርባምንጭ ከተማ፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ቤንጅ ማጂ ቡና ወደ ሶስተኛ ዙር ማለፋቸው ይታወቃል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም