ስፖርት
ማንችስተር ዩናይትድ ሊዮንን ድራማዊ በሆነ ሁኔታ በማሸነፍ ወደ ግማሽ ፍጻሜ አለፈ 
Apr 18, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 9/2017 (ኢዜአ)፦ በዩሮፓ ሊግ ሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታ ማንችስተር ዩናይትድ ሊዮንን 5 ለ 4 አሸንፏል። ማምሻውን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም የተደረገው ጨዋታ በልብ አንጠልጣይ ክስተቶች የታጀበ ነበር። ማኑኤል ኡጋርቴ እና ዲዮጎ ዳሎት በመጀመሪያ አጋማሽ ባስቆጠሯቸው ጎሎች ማንችስተር ዩናይትድ 2 ለ 0 መምራት ችሏል:: ኮረንቲን ቶሊሶ እና ኒኮላስ ታግሊያፊኮ ከእረፍት መልስ ከመረብ ላይ ያሳረፏቸው ግቦች ሊዮንን አቻ አድርገዋል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ሁለት አቻ በመጠናቀቁ ወደ ጭማሪ 30 ደቂቃ አምርቷል። ራያን ቼርኪ በ105ኛው በጨዋታ እና አሌክሳንደር ላካዜት በ110ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ያስቆጠሯቸው ጎሎች ግብ ሊዮንን 4 ለ 2 መሪ አድርጎ ነበር። ይሁንና ብሩኖ ፈርናንዴዝ በ114ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት፣ ኮቢ ሜይኖ በ120ኛው እና ሀሪ ማጓየር በ121ኛው ደቂቃ ያስቆጠሯቸው ግቦች ለማንችስተር ዩናይትድ ጣፋጭ ድል አስገኝቷል። የሊዮኑ ኮረንቲን ቶሊሶ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ዩናይትድ በድምር ውጤት 7 ለ 6 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ማንችስተር ዩናይትድ በግማሽ ፍጻሜው ከአትሌቲኮ ቢልባኦ ጋር ይጫወታል። አትሌቲኮ ቢልባኦ ሬንጀርስን በደርሶ መልስ ውጤት 2 ለ 0 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። በሌሎች ጨዋታዎች ቶተንሃም ሆትስፐርስ ኢንትራክት ፍራንክፈርትን፣ ቦዶ ግሊምት ላዚዮን በድምር ውጤት በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ቦዶ ግሊምት በግማሽ ፍጻሜው ይገናኛሉ። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሚያዚያ ወር መጨረሻ ይካሄዳሉ።
አርሰናል ሪያል ማድሪድን በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አለፈ
Apr 16, 2025 166
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 8/2017(ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተጠባቂ ፍልሚያ አርሰናል ሪያል ማድሪድን በደርሶ መልስ ውጤት በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ማምሻውን በሳንቲያጎ በርናባው ስታዲየም በተደረገው የሁለቱ ቡድኖች የመልስ ጨዋታ አርሰናል 2 ለ 1 አሸንፏል። ቡካዮ ሶካ እና ጋብርኤል ማርቲኔሊ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ቪኒሺየስ ጁኒየር ለሪያል ማድሪድ ከሽንፈት ያላዳነችውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ቡካዮ ሳካ ፍጹም ቅጣት ምት ስቷል።   ውጤቱን ተከትሎ አርሰናል በድምሩ 5 ለ 1 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። የ15 ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሪያል ማድሪድ ጉዞው ሩብ ፍጻሜ ላይ ሲገታ አርሰናል በግማሽ ፍጻሜው ከፒኤስጂ ይጫወታል።   በሳን ሲሮ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታ ኢንተር ሚላን ከባየር ሙኒክ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። ላውታሮ ማርቲኔዝ እና ቤንጃሚን ፓቫርድ ለኢንተር ሚላን ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ሀሪ ኬን እና ኤሪክ ዳየር ለባየር ሙኒክ ግቦቹን ከመረብ ላይ ያሳረፉ ተጫዋቾች ናቸው። ውጤቱን ተከትሎ ኢንተር ሚላን በድምሩ 4 ለ 3 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ሲቀላቀል በግማሽ ፍጻሜው ከባርሴሎና ጋር ይጫወታል። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሚያዚያ ወር መጨረሻ ይደረጋሉ።
የኢትዮጵያ መድን እና አዳማ ከተማ ተጠባቂ መርሃ ግብር
Apr 16, 2025 103
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 8/2017(ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ መድን ከአዳማ ከተማ ጋር ይጫወታል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከቀኑ 9 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ መድን በ45 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ካሸነፈ ከተከታዩ ኢትዮጵያ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ዘጠኝ ከፍ ያደርጋል። በአንጻሩ በ21 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ የሚገኘው አዳማ ከተማ ማሸነፍ ከወራጅነት ቦታ ለመላቀቅ በሚያደርገው ትግል ትርጉም ያለው ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። የ25ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሃ ግብር ድሬዳዋ ከተማ እና ኢትዮ ኤሌክትሪክ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ያገናኛል። ድሬዳዋ ከተማ በ26 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ29 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ማሸነፍ ለሁለቱም ቡድኖች ከወራጅ ስጋት ቀጠና ለመራቅ ያግዛቸዋል። በተያያዘ ዜና ትናንት በተካሄዱ የ25ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና ፋሲል ከነማን፣ መቻል አርባምንጭ ከተማን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
የሎስ ብላንኮዎቹ እና መድፈኞቹ ፍጥጫ
Apr 16, 2025 129
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 8/2017(ኢዜአ):- የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ የመልስ መርሃ ግብር ሪያል ማድሪድ ከአርሰናል ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ የዓለም አግር ኳስ አፍቃሪያንን ቀልብ ገዝቷል። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ከ80 ሺህ በላይ ተመልካች በላይ በሚያስተናግደው ሳንቲያጎ በርናባው ይደረጋል። ባለፈው ሳምንት በተደረገው የመጀመሪያው ዙር ጨዋታ አርሰናል በኤምሬትስ ሪያል ማድሪድን 3 ለ 0 አሸንፏል።   የ15 ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊው ሪያል ማድሪድ በውድድሩ ለመቆየት በዛሬው ጨዋታ ውጤት የመቀልበስ ከባድ ፈተናን ማለፍ ይጠበቅበታል። ማድሪዳውያን ይሄን እናሳካዋለን እያሉ ነው። ሪያል ማድሪድ “ፍጹም የማይቻለውን የማድረግ ተአምራዊ አቅም አለው” አልፎም “የተአምራቶች ቡድን ነው” የሚሉ ሙገሳዎችና አድናቆችን ቢያገኝም ከመድፈኞቹ በጣም የበረታ ፉክክር እንደሚገጥመው ሳይታለም የተፈታ ጉዳይ ነው። አርሰናል በሪያል ማድሪድ እስከ አሁን በሻምፒዮንስ ሊግ ባደረጋቸው ጨዋታዎች ተሸንፎ አያውቅም። በዚሁ ጥሩ ታሪኩ ለመቀጠል 90 ደቂቃዎች ይቀሩታል። ሎስ ብላንኮሶቹ ወይስ መድፈኞቹ? የመጨረሻው ሳቅ የማነው? የሚለው የሁሉም ጥያቄ ነው። የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር የ35 ዓመቱ ፈረንሳዊ ፍራንስዋ ሌቲክሲየርን ተጠባቂውን ፍልሚያ በዋና ዳኝነት እንዲመሩ መድቧቸዋል። በተመሳሳይ ምሽት 4 ሰዓት በሳን ሲሮ ስታዲየም ኢንተርሚላን ከባየር ሙኒክ ይጫወታሉ።   ኢንተርሚላን በመጀመሪያው ጨዋታ 2 ለ 1 ማሸነፉ ይታወቃል። ቡድኑ በአንጻራዊነት ከተጋጣሚው የተሻለ የማለፍ እድል አለው። የ45 ዓመቱ ስሎቬኒያዊ ስላቫኮ ቪንቺች ጨዋታውን በመሐል ዳኝነት ይመሩታል። ትናንት በተደረጉ ጨዋታዎች ቀጥሎ ሲውል ባርሴሎና ቦሩሲያ ዶርትሙንድን፣ ፒኤስጂ አስቶንቪላን በደርሶ መልስ ውጤት በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅለዋል።
የዞን አምስትና የምስራቅ አፍሪካ ወርልድ ቴኳንዶ ውድድር በመጪው ሳምንት በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Apr 15, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2017(ኢዜአ)፦የዞን አምስት እና የምስራቅ አፍሪካ ወርልድ ቴኳንዶ ውድድር ሚያዝያ 14 እስከ 16 ቀን 2017 በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ወርልድ ቴኳንዶ ፌዴሬሽን አስታወቀ። በአፍሪካ ፕሬዝዳንታዊ ውድድር ላይ ከተለያዩ 44 የአለም ሀገራት የተውጣጡ ከ 300 በላይ ልዑካን ቡድን እንደሚሳተፉ ፌዴሬሽኑ አስታውቋል። ፌዴሬሽኑ የምስራቅ አፍሪካ ወርልድ ቴኳንዶ ውድድር እና የአፍሪካ ወርልድ ቴኳንዶ ዩኒየን ጠቅላላ ጉባኤን አስመልክቶ ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ዳዊት አስፋው በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ውድድሩን ለማዘጋጀት ለአንድ አመት ያህል አስፈላጊውን የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ሲያከናውኑ ቆይተዋል። በዞን 5 የምስራቅ አፍሪካ ወርልድ ቴኳንዶ ውድድር ኢትዮጵያ ፣ ብሩንዲ፣ ሩዋን፣ ኬኒያ፣ ሶማሊያ፣ ታንዛኒያ ፣ ኡጋንዳና ጅቡቲ እንደሚሳተፉ ተገልጿል፡፡ ኢትዮጵያ በውድድሩ ለመጀመሪያ ጊዜ የምትሳተፍ መሆኑን ገልፀው በዚህም 26 ተወዳዳሪዎች ተመርጠው በቂ ዝግጅት ሲያደርጉ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። በተጨማሪም 50 በግል የሚወዳደሩ ኢትዮጵያውያን ተሳታፊ እንደሚሆኑ ጠቅሰዋል። ውድድሩ ሚያዝያ 14 ቀን 2017 በኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ እንደሚጀመር አስታውቀው ውድድሩን የሚመሩት አለም አቀፍ እውቅና የተሰጣቸው ኢትዮጵያውያን ዳኞች ብቻ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የአፍሪካ ፕሬዝዳንታዊ ውድድር ሚያዝያ 15 ቀን 2017 የሚካሄድ ሲሆን አምስት ኢትዮጵያውያንና 32 አለም አቀፍ ዳኞች ውድድሩን እንደሚመሩት አስታውቀዋል። በተጨማሪም የአፍሪካ ወርልድ ቴኳንዶ ዩኒየን ጠቅላላ ጉባኤ ሚያዚያ 16 ቀን 2017 እንደሚደረግ ጠቅሰዋል። አህጉር አቀፍ ውድድሩ የወርልድ ቴኳንዶን ለማስተዋወቅ፣ተወዳዳሪዎች አህጉር አቀፍ ልምድ እንዲቀስሙ ለማድረግ እና የሀገርን መልካም ገፅታ ለመገንባት አላማ ያደረገ ነው ብለዋል። እንዲሁም ከስፖርታዊ ውድድሩ ባሻገር ሀገራችን ያለችበትን ሁለንተናዊ ለውጥ ለማስተዋወቅ ትልቅ ሚና እንዳለው ነው ያስታወቁት። ውድድሩ እኤአ በ2028 ለሚደረገው የአለም ወርልድ ቴኳንዶ ውድድር ስፖርተኞችን ብቁ ለማድረግ ከፍተኛ ልምድ የሚወሰድበት እንደሆነም በመግለጫቸው አንስተዋል።
ስፖርት ለሰላም ግንባታ ያለውን አበርክቶ ለማጠናከር የተሰሩ ስራዎች ውጤት እያስገኙ ነው -ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሐመድ
Apr 15, 2025 79
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 7/2017 (ኢዜአ)፦ስፖርት ለሰላም ግንባታ ያለውን አበርክቶ ለማጠናከር የተሰሩ ስራዎች ውጤት እያስገኙ መሆኑን የባህል እና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሐመድ ገለጹ። "ስፖርት ለልማትና ለሠላም" በሚል መሪ ሐሳብ በኦሮሚያ ክልል በቄለም ወለጋ ዞን ደምቢዶሎ ከተማ የማህበረሰብ አቀፍ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ተካሂዷል።   የባህል እና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሐመድ በዚሁ ወቅት፤ በደምቢዶሎ ከተማ የማህበረሰብ አቀፍ የስፖርት እንቅስቃሴ ስፖርት ለልማትና ለሰላም ያለውን አበርክቶ ያሣየ ነው ብለዋል። ስፖርት ንቁና ጤንነቱ የተሟላ ዜጋን ከማፍራት አኳያ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመው፥ መንግስት ለስፖርት ልማት ዕድገት ትልቅ ትኩረት መስጠቱንም ገልጸዋል። በዚህም ስፖርትን ባህል ያደረገ ዜጋን ለማፍራት የተሰሩ ስራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል። በሀገር ዓቀፍ ደረጃ ለ5ኛ ጊዜ የሚከበረውን ስፖርት ለልማትና ለሰላም ቀን በደምቢዶሎ ከተማ መከበሩ ዞኑ ባለፉት ጊዜያት ከነበረበት የሰላም እጦት በሕዝብ እና በመንግስት የጋራ ጥረት መውጣቱን የሚያሳይ ነው ብለዋል። አሁን የተሟላ ሰላም የተገኘበት አካባቢ በመሆኑ ሰላሙን ለማጽናት ስፖርት ትልቅ ሚና እንዳለውም ሚኒስትር ዴኤታው ጠቁመዋል።   የኦሮሚያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ምክትል ቢሮ ሃላፊ ደሣለኝ ጥላሁን በበኩላችው፤ በክልሉ ስፖርትን ባህል ያደረገ ዜጋን ከመፍጠር አኳያ የተሰሩ ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። በክልሉ "አንድ ሄክታር የስፖርት ማዘውተሪያ ለአንድ ቀበሌ" ተብሎ ወደ ስራ የተገባው ኢኒሼቲቭ የማዘውተሪያ ቦታዎችን ችግር እየፈታ መሆኑንም ጠቁመዋል። የቄለም ወለጋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ገመቹ ጉርሜሣ በበኩላቸው፥ በዞኑ የተካሄደው የማህበረሰብ የስፖርት እንቅስቃሴ አከባቢው ሰላማዊ ለመሆኑ ማሣያ መሆኑን ገልጸው፤ስፖርት ለሠላም፣ ለልማት እና አንድነት ያለው ዋጋ በተግባር መታየቱን ጠቁመዋል። በተለያዩ አካባቢዎች ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችን በማሰራት የሚታወቀው ኢንስትራክተር ነጻነት ካሣ እንዳለውም፥ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ አብሮነትና አንድነትን ማምጣት እንደሚችል በተግባር የታየበት ነው ብሏል። ከማህበረሰብ አቀፍ የስፖርት እንቅስቃሴ ተሣታፊዎች መካከል ኢብሳ ደበላ እና ደበላ ተርፋ እንዳሉትም፤ በከተማዋ የስፖርት እንቅስቃሴዎችን ጨምሮ ሌሎች መርሐ ግብሮች መካሄዳቸው ከተማዋ ሰላማዊ ሁኔታ ላይ ለመሆኗ ማሣያ ነው ብለዋል። በዛሬው ዕለት የተካሄደው ስፖርታዊ እንቅስቃሴም ስፖርት ለልማት፣ ለአንድነትና አብሮነት ያለው ከፍተኛ ሚና የታየበት እንደሆነም ጠቁመዋል።
የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ ተጠባቂ የመልስ ጨዋታዎች
Apr 15, 2025 99
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7/2017 (ኢዜአ):- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ። ምሽት 4 ሰዓት ላይ በሲግናል ኡዱና ፓርክ ስታዲየም ቦሩሲያ ዶርትሙንድ ከባርሴሎና የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ጨዋታ ባርሴሎና በሜዳው 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት ማሸነፉ የሚታወስ ነው። 43 ዓመቱ ጣልያናዊ ማውሪዚዮ ማሪያኒ ጨዋታውን በመሐል ዳኝነት ይመሩታል። በተመሳሳይ ምሽት 4 ሰዓት በቪላ ፓርክ ስታዲየም አስቶንቪላ ከፒኤስጂ ይጫወታሉ። ሁለቱ ክለቦች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ባካሄዱት ጨዋታ ፒኤስጂ 3 ለ 1 ማሸነፉ አይዘነጋም። የ41 ዓመቱ ስፔናዊ ሆዜ ማሪያ ሳንቼዝ ሂሜኔዝ የጨዋታው የመሐል ሜዳ አለቃ ናቸው። ባርሴሎና እና ፒኤስጂ ወደ ቀጣዩ ዙር የማለፍ ሰፊ እድል ይዘው ወደ ሜዳ ይገባሉ። ነገ ሪያል ማድሪድ ከአርሰናል እና ኢንተር ሚላን ከባየር ሙኒክ የሚያደርጓቸው የመልስ ጨዋታዎች ተጠባቂ ናቸው።
ናፖሊ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል
Apr 15, 2025 87
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7/2017 (ኢዜአ)፦ በጣልያን ሴሪአ የ32ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ናፖሊ ኢምፖሊን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በዲያጎ አርማንዶ ማራዶና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ስኮት ማክቶሚናይ ሁለት ጎሎችን ሲያስቆጥር ሮሜሎ ሉካኩ ቀሪዋን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ናፖሊ ነጥቡን ወደ 68 ከፍ አድርጓል። ከሊጉ መሪ ኢንተር ሚላን ያለውን ልዩነት ወደ ሶስት ዝቅ ብሏል። ኢምፖሊ በ24 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በሌላ በኩል በስፔን ላሊጋ የ31ኛ ሳምንት ጨዋታ አትሌቲኮ ማድሪድ ሪያል ቫላዶሊድን 4 ለ 2 አሸንፏል። ሁሊያን አልቫሬዝ ሁለት ግቦችን በፍጹም ቅጣት ምት ሲያስቆጥር ጁሊያኖ ሲሞኒ እና አሌክሳንደር ሰርሎዝ ቀሪዎቹን ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ማመዱ ሲያላ በፍጹም ቅጣት ምት እና ዣቪ ሳንቼዝ ለሪያል ቫላዶሊድ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። ውጤቱን ተከትሎ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አትሌቲኮ ማድሪድ ነጥቡን ወደ 63 ከፍ አድርጓል። ሪያል ቫላዶሊድ በ16 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዘዋል። ባርሴሎና በ70 ነጥብ አንደኛ እና ሪያል ማድሪድ በ66 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት ጨዋታ ደግሞ ቦርንማውዝ ፉልሃምን በአንቶዋን ሴሜንዮ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል።
የመላ ደቡብ ወሎ ዞን ስፖርታዊ ጨዋታዎች ተጠናቀቀ
Apr 14, 2025 68
ደሴ፤ ሚያዚያ 6/2017(ኢዜአ)፡- ዘጠነኛው የመላ ደቡብ ወሎ ዞን ስፖርታዊ ጨዋታዎች በተንታ ወረዳ አሸናፊነት ተጠናቀቀ። በደሴ ከተማ ላለፉት አስር ቀናት ሲካሄድ የሰነበተው ዘጠነኛው የመላው ደቡብ ወሎ ዞን የስፖርት ጨዋታ ዛሬ ከሰዓት ተጠናቋል። በዚህም ተንታ ወረዳ በስፖርታዊ ውድድር 11 ወርቅ፣ 11 ብርና 10 ነሐስ በማምጣት አንደኛ በመውጣት አሸናፊ ሆኗል። በስምንት ወርቅ፣ በአንድ ብር እና በአንድ ነሐስ አልቡኮ ወረዳ ሁለተኛ ሲሆን ኩታበር ወረዳ ደግሞ በሰባት ወርቅ፣ በአራት ብር እና በሁለት ነሐስ ሦስተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። የደቡብ ወሎ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ጀማል ሞላ እንደገለፁት ውድድሩ የተቀዛቀዘውን ስፖርት በማነቃቃት የዘርፉን ኢኮኖሚ ለማሳደግ አስተዋጽኦ አለው። ሁሉንም ወረዳዎችና የከተማ አስተዳደሮች በማሳተፍ በተካሄደው የመላ ደቡብ ወሎ ዞን ጨዋታዎች በ13 የስፖርት ዓይነቶች ከ2 ሺህ 500 በላይ ስፖርተኞች መሳተፋቸውን አውስተዋል። በውደድሩ የላቀ ውጤት ያስመዘገቡ ከ300 በላይ ስፖርተኞች ዞኑን ወክለው በመላው አማራ ክልል ጨዋታዎች ላይ እንዲሳተፉ መመረጣቸውንም አስረድተዋል። በስፖርት የእርስ በእርስ ግንኙነትን በማጠናከር ተተኪ ስፖርተኛ ለመፍጠርም እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው በየአካባቢው የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎችም እየተመቻቹ ነው ብለዋል። የተንታ ወረዳ ወጣቶችና ስፖርት ጽህፈት ኃላፊና የልዑኩ አስተባባሪ አቶ ሰለሞን መላኩ በበኩላቸው በውድድሩ የተሻለ ውጤት በማስመዝገባቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። ውድድሩ አንድነታችንን ከማጠናከር ባለፈ ባህልን ለማስተዋወቅ አስችሎናል ብለዋል። በማጠቃለያ ፕሮግራሙ የአማራ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ እርዚቅ ኢሳን ጨምሮ የክልሉ፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አመራሮች፣ የስፖርት ቤተሰቦች፣ ስፖርተኞችና ሌሎች አካላት ተገኝተዋል።  
ስፖርት ለአብሮነት፣ ለልማትና ለዘላቂ ሰላም ያለውን ሚና የማጎልበት ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል - ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሃመድ
Apr 14, 2025 60
አዲስ አበባ ፤ሚያዚያ 6/2017(ኢዜአ):-ስፖርት ለአብሮነት፣ ለልማትና ለዘላቂ ሰላም ግንባታ ያለውን ሚና የማጎልበት ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የባህል እና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሃመድ ገለጹ። 5ኛው ሀገር አቀፍ ስፖርት ለልማትና ለሰላም ቀን በኦሮሚያ ክልል ቄለም ወለጋ ዞን ደምቢዶሎ ከተማ በፓናል ውይይት እየተከበረ ነው።   በውይይቱ የባህል እና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሃመድ፣ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኢሣያስ ጅራ፣ የኦሮሚያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ደሳለኝ ጥላሁን፣ የቄለም ወለጋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ገመቹ ጉርሜሣን ጨምሮ የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች እየተሳተፉ ነው። በውይይቱ ስፖርት ለጤንነት፣ ለልማት፣ ለሰላምና ለአንድነት ያለውን ሚና ለማጠናከር እንደሚሰራ ተጠቁሟል። የባህል እና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ መክዩ መሃመድ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር፤ ስፖርት ለሀገር ብልጽግና መረጋገጥ ሁለንተናዊ ሚናን ይጫወታል ብለዋል። ስፖርት ለዘላቂ ሰላም መረጋገጥ፣ ለልማት እና ለአብሮነት እሴት መጎልበት ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ጠቅሰው፤ በዚህም በሀገር አቀፍ ደረጃ የወንድማማችነት ትርክትን ከማጠናከር አንጻር ትልቅ ድርሻ እየተወጣ ነው ብለዋል። ስፖርት ጤናው የተጠበቀ ዜጋን በመፍጠር የበኩልም ድርሻው ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመዋል። የቄለም ወለጋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ገመቹ ጉርሜሣ በዚሁ ወቅት፤ በዞኑ ለስፖርት እና የባህል እሴቶች መጎልበት ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። በዞኑ ስፖርት ህዝባዊ መሠረት እንዲኖረው እንዲሁም ለሰላምና ልማት አበርክቶውን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። በማህበረሰብ አቀፍ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ እንዲጎለብትም በሁሉም ወረዳዎች እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የኦሮሚያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ምክትል ሃላፊ ደሣለኝ ጥላሁን በበኩላቸው በክልሉ ለስፖርት በተሰጠው ትኩረት በአንድ ቀበሌ አንድ የስፖርት ማዘውተሪያ ኢኒሼቲቭ ተግባራዊ መደረጉን አስታውቀዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ12 ጊዜ በሀገር አቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ5ኛ ጊዜ የሚከበረውን ስፖርት ለልማትና ለሰላም ቀንን ምክንያት በማድረግ በነገው ዕለት በደምቢዶሎ ከተማ የማህበረሰብ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ እንደሚካሄደም ተጠቁሟል።    
የ25ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሃ ግብሮች
Apr 14, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 6/2017(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት ሶስት ጨዋታዎች ዛሬ ይደረጋሉ። ቅዱስ ጊዮርጊስ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ከ30 በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። 16 ጊዜ የሊጉ ዋንጫ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ31 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። የአምናው የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ32 ነጥብ 9ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ከቀኑ 9 ሰዓት ሲዳማ ቡና ከባህር ዳር ከተማ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሲዳማ ቡና በ29 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ሲይዝ ባህር ዳር ከተማ በ37 ነጥብ 2ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የዕለቱ የመጨረሻ መርሃ ግብር ምሽት 12 ሰዓት ላይ ሃዋሳ ከተማ እና ወላይታ ድቻን ያገናኛል። ሃዋሳ ከተማ በ21 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ወላይታ ድቻ በ37 ነጥብ ተመሳሳይ ነጥብ ባለው ባህር ዳር ከተማ በግብ ክፍያ ተበልጦ 3ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። መርሃ ግብሮቹ በዋንጫ ፉክክሩ እና ላለመውረድ በሚደረገው ፉክክር ውስጥ እጅግ ወሳኝ የሚባሉ ጨዋታዎች ናቸው። በተያያዘ ዜና በተደረጉ የ25ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች መቀሌ 70 እንደርታ ሀድያ ሆሳዕናን 2 ለ 0 ሲያሸንፍ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ስሑል ሽሬ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም