ቀጥታ፡
ስፖርት
በፕሪሚየር ሊጉ ሸገር ከተማ ድል ሲቀናው ፋሲል ከነማ እና ድሬዳዋ ከተማ አቻ ተለያይተዋል 
Nov 22, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሰባተኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ጨዋታዎች መካሄዳቸውን ቀጥለዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሸገር ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። አምበሉ ሄኖክ አዱኛ በ97ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል በፍጹም ቅጣት ምት አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ድሉን ያስመዘገበው ሸገር ከተማ በስምንት ነጥብ ደረጃውን ከ17ኛ ወደ 14ኛ ከፍ አድርጓል።   በአንጻሩ በሊጉ ሶስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በሶስት ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ አላሸነፈም። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሃ ግብር ፋሲል ከነማ እና ድሬዳዋ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ውጤቱን ተከትሎ ፋሲል ከነማ በ12 ነጥብ አራተኛ፣ ድሬዳዋ ከተማ በ10 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዘዋል።   ፋሲል ከነማ የሊጉ መሪ የመሆን እድሉን ሳይጠቀምበት ቀርቷል። በአሁኑ ሰዓት ባህር ዳር ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን እያደረጉ ነው።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሰባተኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል 
Nov 22, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሰባተኛ ሳምንት ዛሬ በሚደረጉ አራት ጨዋታዎች ፍጻሜውን ያገኛል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ምድረገነት ሽሬ ከመቻል በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረገነት ሽሬ በሊጉ ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በበኩሉ ከአምስት ጨዋታዎች ሶስቱን ሲያሸንፍ በሁለቱ አቻ ወጥቷል። ስምንት ግቦችን ሲያስቆጥር ሶስት ግቦች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ11 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በሌላኛው መርሃ ግብር ፋሲል ከነማ ከድሬዳዋ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ፋሲል ከነማ በሊጉ ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር ያስተናገደው አንድ ግብ ብቻ ነው። ቡድኑ በ11 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በበኩሉ በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው አምስት ጨዋታዎች ሶስቱን በድል ሲያጠናቅቅ ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ ስድስት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ድሬዳዋ በዘጠኝ ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ምሽት 12 ሰዓት ላይ ባህር ዳር ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ጨዋታቸውን ያካሂዳሉ። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። አንድ ጊዜ ሲሸነፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ አምስት ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በስድስት ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በበኩሉ ከአምስት ጨዋታዎች ሶስት ጊዜ ድል ሲቀናው ሁለት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር አንድ ጎል ተቆጥሮበታል። ቡድኑ በ11 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ከቀኑ 9 ሰዓት አርባምንጭ ከተማ ከሸገር ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። አርባምንጭ ከተማ በሶስት ነጥብ 17ኛ፣ ሸገር ከተማ በአምስት ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዘዋል።
በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ኒውካስትል ዩናይትድ ከማንችስተር ሲቲ በርንሌይ ከቼልሲ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ 
Nov 22, 2025 107
አዲስ አበባ፤ ህዳር 13/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ከዓለም አቀፍ ጨዋታዎች በኋላ ዛሬ በ12ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ይመለሳል። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ኒውካስትል ዩናይትድ ከማንችስተር ሲቲ በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኒውካስትል ዩናይትድ በ12 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ በ22 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።   ማንችስተር ሲቲ ካሸነፈ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አንድ ዝቅ ያደርጋል። በአንጻሩ ኒውካስትል ከተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርገው ወሳኝ ጨዋታ ነው። ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 ላይ በርንሌይ ከቼልሲ በተርፍ ሙር ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በርንሌይ በ10 ነጥብ 17ኛ፣ ቼልሲ በ20 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ጨዋታው በርንሌይ ከሁለት ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ቼልሲ በድል ጉዞው ለመቆየት የሚያደርጉት ነው።   የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል ከኖቲንግሃም ፎረስት ምሽት 12 ላይ ጨዋታውን ያደርጋል። ሊቨርፑል በ18 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ኖቲንግሃም ፎረስት በዘጠኝ ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቀያዮቹ ወደ ዋንጫው ፉክክር ለመመለስ የዛሬውን ጨዋታ ማሸነፍ ይጠበቅባቸዋል። ኖቲንግሃም ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና እንዲወጣ ያስችለዋል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ቦርንማውዝ ከዌስትሃም ዩናይትድ፣ ዎልቭስ ከክሪስታል ፓላስ፣ ብራይተን ከብሬንትፎርድ እና ፉልሃም ከሰንደርላንድ በተመሳሳይ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
የ2029 የአፍሪካ ዋንጫን ለማዘጋጀትና አሸናፊ ብሔራዊ ቡድን ለመገንባት ተስፋ ያላቸው ታዳጊዎች ወደ እግር ኳሳችን እየመጡ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Nov 21, 2025 150
አዲስ አበባ፤ ህዳር 12/2018(ኢዜአ)፦ የ2029 የአፍሪካ ዋንጫን ለማዘጋጀትና አሸናፊ ብሔራዊ ቡድን ለመገንባት ተስፋ ያላቸው ታዳጊዎች ወደ እግር ኳሳችን እየመጡ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው እዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገ ጨዋታ ከሶማሊያ ቡድን ጋር 3 ለ 3 አቻ የወጣውን ከ17 ዓመት በታች ቡድን ከጨዋታው በኋላ በአካል ተገኝቼ አበረታትቻለሁ ብለዋል። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን እንድታዘጋጅ ያቀረቡትን ይፋዊ ጥያቄ ተከትሎ መንግሥት በየአካባቢው ከትናንሽ እስከ ግዙፍ ስታዲየሞችን እየገነባ ይገኛል ነው ያሉት። ከመሠረተ ልማት ባሻገር ደግሞ የኢትዮጵያውያንን እግርኳስ ወዳድነት የሚመጥን እና መልካም ስማችንን ከፍ የሚያደርግ ብሔራዊ ቡድን ለመገንባት የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተጀምረዋል ብለዋል። "የጉዞ 2029 ፕሮጀክት" የሆነው ከ17 ዓመት በታች ቡድናችንም ትልቅ ተስፋ ያለውና የኢትዮጵያ ወጣቶችና ታዳጊዎች ኳስ ጨዋታ እንደሚችሉ፣ እንዲሁም ለአህጉራዊ ዋንጫው ከታች የጀመርነው ዝግጅትም ፍሬ እያፈራ መሆኑን ተመልክተንበታል ነው ያሉት በመልዕክታቸው። ለቡድኑ እዚህ መድረስ አስተዋጽዖ ላበረከቱ ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን፣ ለኮቺንግ ስታፍ አባላት፣ ለእግር ኳስ ፌዴሬሽን አመራሮች እና ለባህልና ስፖርት ሚኒስቴር አመራሮች ምስጋና ለማቅረብ እፈልጋለሁ ብለዋል። የታዳጊ ቡድኑ አባላት በስካሁኑ የውድድር ሂደት ላስመዘገባችሁት ወጤት በርቱ ማለት እፈልጋለሁ ሲሉም ገልጸዋል።
ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ኢትዮጵያ እና ሶማሊያ አቻ ተለያዩ
Nov 21, 2025 99
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 12/2018(ኢዜአ)፦ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ የምድብ አንድ ጨዋታ አዘጋጇ ኢትዮጵያ ከሶማሊያ ጋር ባደረገችው ጨዋታ ሶስት አቻ ተለያይታለች። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ዳዊት ካሳው በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ሁለት ግቦችን አስቆጥሯል። አቤኔዘር አለማየሁ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ኑርአብዲራሺድ ለሶማሊያ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ቢላል ዩሱፍ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ በሰባት ነጥብ የምድብ መሪነቷን አጠናክራለች። ሶማሊያ በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዛለች። የኢትዮጵያው አጥቂ ዳዊት ካሳው በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ ስድስት ከፍ በማድረግ ተመሳሳይ የግብ መጠን ካስቆጠረው ከታንዛንያው ሉክማን አሊ ጋር የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በጋራ እየመራ ነው። በምድብ አንድ ዛሬ በተደረገ ሌላኛው ጨዋታ ኬንያ ሩዋንዳን 2 ለ 1 አሸንፋለች።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ልደታ ክፍለ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ አዲስ አበባ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ይጫወታሉ 
Nov 21, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 12/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሰባተኛ ሳምንት ዛሬ በሚደረጉ ሁለት ጨዋታዎች ፍጻሜውን ያገኛል። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ልደታ ክፍለ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ በኢትዮጵያ ንግድ ሜዳ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ልደታ ክፍለ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው ስድስት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሶስት ጊዜ ሲሸነፍ ሁለት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። በጨዋታዎቹ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር 10 ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በአምስት ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚዋ ሃዋሳ ከተማ በውድድር ዓመቱ እስከ አሁን ባከናወናቸው ስድስት ጨዋታዎች በአራቱ ድል ሲቀናው ሁለት ጊዜ ተሸንፏል። 11 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ስድስት ግቦች ተቆጥረውበታል። ሃዋሳ ከተማ በ12 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። በሌላኛው መርሃ ግብር አዲስ አበባ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሜዳ ይጫወታሉ። አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው ስድስት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በጨዋታዎቹ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር 13 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በሶስት ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በውድድር ዓመቱ ካካሄዳቸው ስድስት ጨዋታዎች መካከል ያሸነፈው በአንድ አጋጣሚ ብቻ ነው። አራት ጊዜ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ተለያይቷል። አርባምንጭ ከተማ በአራት ነጥብ 13ኛ ደረጃን በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ሁለቱ ቡድኖች በሊጉ ሁለተኛ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሰባተኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታዎች
Nov 21, 2025 98
አዲስ አበባ፤ ህዳር 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሰባተኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ።’ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሀዲያ ሆሳዕና በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በውድድር ዓመቱ እስከ አሁን ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አራቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በጨዋታዎቹ ስድስት ግቦችን ሲያስቆጥር ሁለት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ12 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሀዲያ ሆሳዕና በሊጉ ባከናወናቸው አምስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሁለት ጊዜ ሲሸነፍ ሶስት ጊዜ አቻ ተለያይቷል። ሶስት ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ስድስት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ሀዲያ ሆሳዕና በሶስት ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ጨዋታው ቅዱስ ጊዮርጊስ በድል ጉዞ ለመቀጠል፣ ሀዲያ ሆሳዕና በውድድር ዓመቱ የመጀመሪያ ድሉን ለማሳካት የሚያደርጉት ነው። በተያያዘም በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ኢትዮጵያ ቡና ከኢትዮጵያ መድን ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ኢትዮጵያ ቡና በሊጉ ካደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች መካከል ማሸነፍ የቻለው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። ሶስት ጊዜ ሲሸነፍ አንድ ጊዜ አቻ ወጥቷል። ቡናማዎቹ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አራት ግቦችን አስተናግዷል። ቡድኑ በአራት ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን ካካሄዳቸው አራት ጨዋታዎች በአንዱ ድል ሲቀናው በተመሳሳይ አንድ ጊዜ ተሸንፏል። ሁለት ጊዜ አቻ ወጥቷል። ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር በተመሳሳይ ሁለት ግቦች ተቆጥረውበታል። መድን አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በአምስት ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከሃዋሳ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 10 በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም