ቀጥታ፡
ስፖርት
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫው ያልፍ ይሆን? 
Jul 12, 2026 401
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2018 (ኢዜአ)፦ ለ2026 የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የሚጫወተው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን፣ ወሳኙንና የመጨረሻውን የዙር መልስ ጨዋታ ዛሬ ከዛምቢያ ጋር ያካሂዳል። ጨዋታው ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይከናወናል። ሁለቱ ሀገራት ሰኔ 27 ቀን 2018 ዓ.ም በንዶላ ሌቪ ምዋናዋሳ ስታዲየም ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛምቢያ 2 ለ 1 አሸንፋለች። ፍሪዳ ንዳሼ እና ፒዳ ሙዙዋ የዛምቢያን ጎሎች አስቆጥረዋል። ምኅረት አየለ የኢትዮጵያን ብቸኛ ግብ ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ጨዋታው በዛምቢያ የተደረገ ቢሆንም፣ የኢትዮጵያ ታዳጊዎች ከሜዳቸው ውጪ ያስቆጠሯት ወሳኝ ጎል በአዲስ አበባው የመልስ ጨዋታ የማለፍ ዕድላቸው እንዲለመልም አድርጎታል። በአሰልጣኝ ራውዳ አሊ የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከመጀመሪያው ጨዋታ መልስ ዝግጅቱን በአዲስ አበባ ሲያደርግ ቆይቷል። ቡድኑ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ያከናወነ ሲሆን ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት እና የስነ ልቦና ዝግጁነት ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በልምምዱ ላይ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ምክትል ኘሬዝዳንት ዳኛቸው ንግሩ (ዶ/ር)፣ የፌዴሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ባሕሩ ጥላሁን፣ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል ወይዘሪት ብዙዓየሁ ጀምበሩ እና የካፍ ኤሊት ኢንስትራክተር አብርሃም መብራቱ በመገኘት ቡድኑን አበረታተዋል። ኢትዮጵያ በድምር ውጤት ካሸነፈች በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ ለፊፋ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ ማለፏን ታረጋግጣለች። በአንጻሩ ዛምቢያ ማሸነፍ ወይም አቻ መውጣት ከቻለች ለሦስተኛ ተከታታይ ጊዜ በዓለም ዋንጫው መሳተፏን ታረጋግጣለች። በርካታ ደጋፊ በስታዲየሙ በመገኘት ለታዳጊ ብሔራዊ ቡድኑ ድጋፍ ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል። በሞሮኮ አስተናጋጅነት በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም ለሚካሄደው 10ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ዓለም ዋንጫ 24 አገራት ይሳተፋሉ። የአፍሪካ አህጉር በውድድሩ ላይ በአምስት አገራት የምትወከል ሲሆን፣ ከአስተናጋጇ ሞሮኮ ውጪ አህጉሪቱን ወክለው ወደ ዓለም ዋንጫው የሚጓዙት ቀሪዎቹ አራት አገራት በመጨረሻው ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች ተለይተው ይታወቃሉ።
የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገፅታ ከመቀየር ባለፈ ለስፖርቱ ዘርፍ ትልቅ መነቃቃት ፈጥሯል - ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን
Jul 12, 2026 398
አሶሳ፤ ሐምሌ 5/2018 (ኢዜአ)፡- የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለስፖርቱ ዘርፍ ትልቅ መነቃቃት መፍጠሩን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ገለጹ። የአሶሳ ከተማ የመጀመሪያው የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ "ለኮሪደር ልማትና ለከተማ ውበት እሮጣለሁ" በሚል መሪ ሃሳብ ዛሬ ማለዳ ተካሂዷል።   በመርሃግብሩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ የአሶሳ ከተማ ነዋሪዎች ተገኝተዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን በወቅቱ እንደተናገሩት፤ የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገፅታ በመቀየር የተለያዩ አገልግሎቶች ለነዋሪዎች ተደራሽ እንዲሆኑ አድርጓል። የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማትም ከተማዋን በማዘመን ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትሆን ከማድረግ ባለፈ በርካታ የስፖርት ማዘውተሪያ በታዎችን በመገንባት ለዘርፉ ትልቅ መነቃቃት መፍጠሩን ገልጸዋል።   በዚህም የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያሳተፈ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ በተለዬ ሁኔታ እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመው፥ የዛሬው የጎዳና ላይ ሩጫም የኮሪደር ልማቱ ለስፖርቱ የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ ይበልጥ የሚያመላክት ነው ብለዋል የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ኢብራሂም መንሱር በበኩላቸው፤ መንግስት ለስፖርቱ ዘርፍ በሰጠው ትኩረት በርካታ የስፖርት መሠረተ ልማቶች እየተገነቡ መሆኑን አንስተዋል። እንደዚህ ዓይነት የጎዳና ላይ ሩጫ የአትሌቲክስ ስፖርትን ከማነቃቃት ባለፈ በህዝቦች መካከል ያለውን ማህበራዊ ትስስር ለማጠናከር እንደሚያግዝም ጠቁመዋል።   በውድድሩ አሸናፊ ለሆኑ ሯጮችም ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።  
የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ያዘጋጀው የ5 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር እየተካሄደ ነው
Jul 12, 2026 1148
አዲስ አበባ ፤ሐምሌ 5 /2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ያዘጋጀው የ5 ኪሎ ሜትር ታላቁ የሩጫ ውድድር በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ እየተካሄደ ይገኛል። "ኢትዮጵያ እየመከረች ነው" በሚል መሪ ሃሳብ በመስቀል አደባባይ እየተካሄደ ባለው በዚህ መርሃ ግብር ላይ ሴቶች፣ ሕፃናትና ወጣቶችን ጨምሮ በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች በመሳተፍ ላይ ናቸው። በአሁኑ ወቅትም የውድድሩ ተሳታፊዎች ከሩጫው አስቀድሞ በተዘጋጀው የጋራ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ላይ በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። የኢትዮጵያ ዋናው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ከመጪው ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባ የሚካሄድ ሲሆን፤ በዋናው ጉባኤ ላይ የሚሳተፉ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር የሕዝብ ወኪሎችም ወደ አዲስ አበባ በመግባት ላይ ናቸው። በዚህ ዋና የምክክር ጉባኤ ላይ፡ • የሀገር ግንባታ፣ • የመንግሥት አደረጃጀትና ቅርጽ፣ • የፖለቲካ ሥርዓት፣ ውክልና እና የምርጫ ሥርዓት፣ • የፌዴራል ከተሞች (አዲስ አበባና ድሬዳዋ) ጉዳይ፣ • የሃይማኖት ጉዳዮች፣ • የተቋማት ግንባታ፣ የሕግ የበላይነትና ሰብዓዊ መብቶች፣ • ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች (የአርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች ጉዳይን ጨምሮ)፣ • እንዲሁም ሙስና፣ መልካም አስተዳደርና የሰላም ግንባታን ያካተቱ ስምንት ዐበይት አጀንዳዎች ላይ የሕዝብ ወኪሎች የሚመክሩባቸው ይሆናል። በመስቀል አደባባይ በተሰናዳው በዚህ የአምስት ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር መርሃ ግብር ላይ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አቶ አዝመራው አንደሞ፣ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ እንዲሁም የኮሚሽኑ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ኮሚሽነሮች ተገኝተዋል።
አርጀንቲና ስዊዘርላንድን በመርታት ለግማሽ ፍጻሜ አለፈች
Jul 12, 2026 407
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር አርጀንቲና ስዊዘርላንድን 3 ለ 1 አሸንፋለች። ማለዳ ላይ በተጠናቀቀው እና በካንሳስ ሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አሌክሲስ ማካሊስተር በ10ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል አርጀንቲናን መሪ አድርጓል። የ39 ዓመቱ ሊዮኔል ሜሲ ለግቧ መቆጠር ምክንያት ሆኗል። ሊዮኔል ሜሲ በዓለም ዋንጫ ታሪክ 10 ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ ያቀበለ የመጀመሪያ ተጫዋች ሆኗል። ዳን ንዶይ በ67ኛው ደቂቃ የስዊዘርላንድን የአቻነት ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ንዶይ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ሁለተኛ ጎሉን አስቆጥሯል። የ27 ዓመቱ የስዊዘርላንድ አጥቂ ብሬል ኢምቦሎ በ72ኛው ደቂቃ በሁለተኛ ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ኢምቦሎ ሁለተኛ ቢጫ ካርድ የተመለከተው በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ አታሎ ወድቋል በሚል በተላለፈ ውሳኔ ምክንያት ነው። ቢጫውን መጀመሪያ ያየው የአርጀንቲናው ሊያንድሮ ፓሬዴስ ሲሆን ውሳኔው ተሰርዞ ኢምቦሎ በቀይ ካርድ እንዲወጣ ተደርጓል። ኢምቦሎ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ሁለት ጎሎችን አስቆጥሯል። በፊፋ አዲሱ ሕግ አንድ ተጫዋች ቢጫ ካርድ ያለበት ተጫዋች ካታለለ ቀይ ካርድ እንደሚመለከት ይደነግጋል። ውሳኔው ስዊዘርላንዶችን አላስደስተም። ጨዋታው በመደበኛው ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት በማለቁ ምክንያት 30 ደቂቃ ተጨምሯል። ሁሊያን አልቫሬዝ 112ኛው ደቂቃ በግሩም ሁኔታ ባስቆጠረው ጎል አርጀንቲና መሪ ሆናለች። ተቀይሮ የገባው ላውታሮ ማርቲኔዝ በ121ኛው ደቂቃ የአርጀንቲናን አሸናፊነት ያረጋገጠችውን ጎል አስቆጥሯል። በውድድሩ ላይ ሁለተኛ ግቡን ከመረብ ላይ አሳርፏል። አልቫሬዝ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከቀይ ካርዱ በኋላ በጥልቀት በመከላከል ጨዋታውን ወደ መለያ ምት የመውሰድ እቅድ የነበራት ስዊዘርላንድ ውጥኗ አልተሳካም። ለሜሲ የዛሬ መርሐ ግብር በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ግብ ያላስቆጠረበት የመጀመሪያ ጨዋታ ሆኗል። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የዓለም ዋንጫ ሻምፒዮን አርጀንቲና ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። በዓለም ዋንጫ ተሳትፎዋ አምስተኛ ጊዜ ለግማሽ ፍጻሜ የደረሰችው አርጀንቲና ለፍጻሜ ለማለፍ ከእንግሊዝ ጋር የምታደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ስዊዘርላንድ ለመጀመሪያ ጊዜ ግማሽ ፍጻሜ የማለፍ ውጥኗ ሳይሳካ ቀርቷል። ጨዋታውን ተከትሎ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ተጠናቋል። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ሐምሌ 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳሉ። ፈረንሳይ ከስፔን፣ አርጀንቲና ከእንግሊዝ ለፍጻሜ ለማለፍ ይፋለማሉ።
እንግሊዝ ኖርዌይን በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አለፈች
Jul 12, 2026 301
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታ እንግሊዝ ኖርዌይን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ከእኩለ ሌሊት በኋላ በሚያሚ በተደረገው ጨዋታ አንድሪያስ ሼልድሩፕ በ36ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል ኖርዌይን መሪ አድርጓል። ጁድ ቤሊንግሃም በመጀመሪያው አጋማሽ ማብቂያ የእንግሊዝን የአቻነት ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቶርብዮን ሄገም በ56ኛው ደቂቃ ኖርዌይን መሪ ቢያደርግም በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ አርሊንግ ሃላንድ የማዕዘን ምት ከመመታቱ በፊት ኤሊዮት ሄንደርሰን ላይ በሰራው ጥፋት ጎሉ ተሽሯል። ጨዋታው በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት በመጠናቀቁ ምክንያት ወደ 30 ደቂቃ አምርቷል። ጁድ ቤሊንግሃም በ93ኛው ደቂቃ ለእንግሊዝ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። የኖርዌይ ግብ ጠባቂ ኦርጃን ኒላንድ ስህተት ለግቧ መቆጠር ከፍተኛ ድርሻ ወስዷል። በጨዋታው ሁለት ግቦችን ያስቆጠረው የ23 ዓመቱ ቤሊንግሃም በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ከመረብ ላይ ጎሎች ብዛት ስድስት አድርሷል። ቤሊንግሃም ከቡድን አጋሩ ሃሪ ኬን ጋር በተመሳሳይ ስድስት ጎሎችን በዓለም ዋንጫው አስቆጥሯል። በጨዋታው እንግሊዝ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ብትወስድም ኖርዌይ ግልጽ የግብ እድሎች በመፍጠር የተሻለች ነበረች። ኖርዌይ በሁለተኛው አጋማሽ የወሰደችውን ብልጫ ወደ ግብ መቀየር አልቻለችም። ውጤቱን ተከትሎ እንግሊዝ ለመጀመሪያ ጊዜ ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። አራት ውስጥ ስትገባ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። ለፍጻሜ ለማለፍ ከአርጀንቲና ስዊዘርላንድ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። የሰሜን አውሮፓዋ ኖርዌይ ለመጀመሪያ ጊዜ ለግማሽ ፍጻሜ የማለፍ ህልሟ ሳይሳካ ቀርቷል። ኖርዌይ በዓለም ዋንጫው ላይ የነበራት መልካም ግስጋሴ ሩብ ፍጻሜው ላይ ተገቷል። ሰባት ጎሎቹን ያስቆጠረው የኖርዌው አርሊንግ ሃላንድ ከከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት ፉክክሩ ውጪ ሆኗል። ከሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በፊት በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ለደቡብ አፍሪካ የተጫወተው እና ዛሬ ህይወቱ ያለፈው የ25 ዓመቱ ጄይደን አዳምስ የሕሊና ፀሎት ተደርጓል። ከሌሊቱ 10 ሰዓት ላይ አርጀንቲና ከስዊዘርላንድ በካንሳስ ሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
አስተዳደሩ በአዲሱ በጀት ዓመት ተተኪ ስፖርተኞችን ማፍራት ለሚያስችሉ ተግባራት ትኩረት ይሰጣል
Jul 11, 2026 359
ደብረብርሃን፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር በአዲሱ በጀት ዓመት ተተኪ ስፖርተኞችን ማፍራት ለሚያስችሉ ተግባራት ትኩረት እንደሚሰጥ አስታወቀ። የደብረ ብርሃን ከተማ ስፖርት ምክር ቤት የ2019 በጀት ዓመት እቅድ ላይ የሚመክር ጉባኤውን ዛሬ አካሂዷል። የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባና የስፖርት ምክር ቤቱ ሰብሳቢ በድሉ ውብሸት በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ከተማዋ በኢንዱስትሪ፣ ቱሪዝምና ኢንቨስትመት ተመራጭ እየሆነችና እያደገች ትገኛለች።   በአዲሱ በጀት ዓመትም ይሕንኑ እድገት በተሟላ መልኩ ለማስቀጠል ስድስት ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች እንደሚገነቡ ገልጸዋል። ስፖርት ወጣቶችን በስብዕና ለመገንባት፣ ጤናማና አምራች ዜጋ ለመፍጠር የሚያግዝ በመሆኑ ባለሃብቱና ማሕበረሰቡ በመሰረተ ልማት ግንባታው በንቃት እንዲሳተፍ ነው የጠየቁት። የከተማ አስተዳደሩ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ ተክለዮሃንስ ኃይለጊዮርጊስ በበኩላቸው፤ የስፖርት ዘርፉን በመደገፍ ብቁና ተወዳዳሪ ሰፖርተኞችን ለማፍራት ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። ምክር ቤቱ በ2019 በጀት ዓመት ለሚካሄዱ የስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታዎች ከ27 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ማጽደቁን ገልጸዋል። በከተማ አስተዳደሩ 12 ካርታና ፕላን ያላቸው የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች መኖራቸውም ነው የተገለፀው።
የማስ ስፖርት መጠናከር የዜጎችን የአብሮነት እሴት ያጎለብታል
Jul 11, 2026 542
ሐረር፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የማስ ስፖርት እንቅስቃሴዎች መጠናከር ጤናማ ትውልድ እንዲኖር ከማስቻል ባለፈ የዜጎችን የአብሮነት እሴት የሚያጎለብት መሆኑን የሐረሪ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ገለጸ። በሐረር ከተማ በሚገኘው የአባድር ፕላዛ መናፈሻ ስፍራ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ተካሄዷል።   ከጠዋቱ 12 ሰዓት ጀምሮ በተከናወነው በዚህ መርሃ ግብር ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ አዘጋጆች፣ የሴክተር መስሪያ ቤት ሰራተኞች፣ ወጣቶች፣ ህጻናትና በርካታ የከተማዋ ነዋሪዎች ተገኝተዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ሙራድ አብዲ፤ የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ለአካል ጥንካሬ፣ ለአእምሮ እድገት እንዲሁም ጤናማና ብቁ ዜጋን ለማፍራት ያለውን ጠቀሜታ አብራርተዋል።   የክልሉ መንግስት 'ስፖርት ለሁሉም፣ በሁሉም ስፍራ' በሚል መርህ በትኩረት እየሰራ መሆኑንም አንስተዋል። የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ከጤና ጥቅሙ ባለፈ የዜጎችን የአብሮነት እሴት የሚያጎለብትና በራሱ የሚተማመን ትውልድ ለመቅረጽ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። መሰል ስፖርታዊ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ኮሚሽነሩ አስገንዝበዋል። የሐረሪ ክልል ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሚ አብዱልዋሲ በበኩላቸው፤ በክልሉ የቱሪዝም ዘርፉን ለማሳደግ ሰፋፊ የኮሪደር ልማትና የቅርስ ጥበቃ ስራዎች በስፋት ተከናውነዋል ብለዋል።   እነዚህ ስራዎች አደጋ ተደቅኖባቸው የነበሩ ቅርሶችን ለመታደግ ከማስቻላቸው ባለፈ፣ ሐረርን ለነዋሪዎቿና ለጎብኚዎቿ ይበልጥ ውብ፣ ሳቢና ማራኪ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል። ኮሚሽነሩ አክለውም፣ በክልሉ መጪው ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም “ሩጫ በህያው ሙዚየም” በሚል መሪ ሀሳብ ሀገር አቀፍ የሩጫ ውድድር እንደሚካሄድ ጠቁመው፤ የዛሬው የአካል ብቃት እንቅስቃሴም የዚሁ ትልቅ ስፖርታዊ ክስተት ማሟሟቂያና የስፖርት ቱሪዝምን የማስተዋወቂያ አካል መሆኑን ተናግረዋል።
አርጀንቲና ከስዊዘርላንድ፣ ኖርዌይ ከእንግሊዝ፤ ግማሽ ፍጻሜ ለመግባት የሚደረጉ ተጠባቂ ፍልሚያዎች
Jul 11, 2026 594
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ የሚገቡ ቀሪ ሁለት ሀገራት የሚለዩባቸው የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። ከሌሊቱ 10 ሰዓት አርጀንቲና ከስዊዘርላንድ በካንሳስ ሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አርጀንቲና 16 ውስጥ ግብጽን 3 ለ 2 በመርታት ወደ ሩብ ፍጻሜው ገብታለች። የወቅቱ የዓለም ዋንጫ ባለቤት አርጀንቲና በጨዋታው እስከ 80ኛው ደቂቃ 2 ለ 0 ብትመራም በ13 ደቂቃዎች ውስጥ ውጤቱን በመቀልበስ አሸንፋለች። የደቡብ አሜሪካዋ ሀገር በውድድሩ ተሳትፎ ታሪኳ ለ10ኛ ጊዜ ሩብ ፍጻሜ ገብታለች። ተጋጣሚዋ ስዊዘርላንድ ኮሎምቢያን በመለያ ምት 4 ለ 3 በማሸነፍ ከ72 ዓመታት በኋላ ወደ ሩብ ፍጻሜው ገብታለች። ጨዋታው በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ እና 30 ደቂቃ ግብ አልተቆጠረበትም። ስዊዘርላንድ ስምንት ውስጥ ስትገባ የአሁኑ ለአራተኛ ጊዜ ነው። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫው ከዚህ ቀደም አንድ ጊዜ ተገናኝተዋል። እ.አ.አ በ2014 በብራዚል በተካሄደው 20ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ 16 ወስጥ ተገናኝተው አርጀንቲና በሊዮኔል ሜሲ ጎል 1 ለ 0 ስዊዘርላንድን በማሸነፍ ወደ ሩብ ፍጻሜው አልፋለች። ቡድኖቹ ከ12 ዓመታት በኋላ በመድረኩ በድጋሚ ተገናኝተዋል። ሁለቱ ሀገራት በውድድሮች እና የወዳጅነት ጨዋታዎች ሰባት ጊዜ ተገናኝተው አርጀንቲና አምስቱን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዛለች። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ስዊዘርላንድ እስከ አሁን አርጀንቲናን አሸንፋ አታውቅም። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ 8 ግቦችን ያስቆጠረው የ39 ዓመቱ አርጀንቲናዊ ሊዮኔል ሜሲ፣ የውድድሩን ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት እየመራ ይገኛል። ሜሲ በዓለም ዋንጫው በአጠቃላይ 21 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪም ነው። አርጀንቲናዊው ኮከብ በዛሬው ጨዋታ ልዩነት ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል። በዓለም ዋንጫው ለስዊዘርላንድ አራት ግቦችን ያስቆጠረው የ29 ዓመቱ ብሬል ኢምቦሎ፣ በዚህ ጨዋታ ላይ ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው ቁልፍ ተጫዋች ነው። በሌላኛው የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ኖርዌይ ከእንግሊዝ በሚያሚ ስታዲየም ከሌሊቱ ስድስት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በ16ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ኖርዌይ ባልተጠበቀ ሁኔታ ብራዚልን 2 1 ለ በመርታት በታሪኳ በዓለም ዋንጫ ለመጀመሪያ ጊዜ አልፋለች። ተጋጣሚዋ እንግሊዝ ከአዘጋጅ ሀገራት መካከል አንዷ በሆነችው ሜክሲኮ በተፈተነችበት ጨዋታ 3 ለ 2 በማሸነፍ ስምንት ውስጥ ገብታለች። ሶስቱ አናብስቶች በዓለም ዋንጫ ተሳትፏቸው ወደ ሩብ ፍጻሜ ሲያልፉ የአሁኑ ለ10ኛ ጊዜ ነው። የአውሮፓ ሀገራቱ ከዚህ ቀደም በዓለም ዋንጫው ተገናኝተው አያውቁም። በተለያዩ ውድድሮች እና የወዳጅነት ጨዋታዎች ላይ 12 ጊዜ ተገናኝተው እንግሊዝ ሰባት ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ስትይዝ ኖርዌይ በሁለት ጨዋታዎች ድል ቀንቷታል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ላይ አቻ ተለያይተዋል። እንግሊዝ በ12ቱ ጨዋታዎች ላይ 28 ጎሎችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ ኖርዌይ ሰባት ግቦችን አስቆጥራለች። እ.አ.አ በ1937 ለመጀመሪያ ጊዜ በተገናኙበት ጨዋታ እንግሊዝ 6 ለ 0 ማሸነፏን መረጃዎች ያመለክታሉ። በዓለም ዋንጫው ላይ ሰባት ጎሎችን ያስቆጠረው የኖርዌው አርሊንግ ሃላንድ እና ስድስት ግቦችን ከመረብ ላይ ያሳረፈው እንግሊዛዊው ሃሪ ኬን በዛሬው ጨዋታ ልዩነት ይፈጥራሉ ተብለው የሚጠበቁ ተጫዋቾች ናቸው። የኖርዌው አምበል ማርቲን ኦዴጋርድ እና የእንግሊዙ ጁድ ቤሊንግሃም መሐል ክፍል ላይ የሚኖራቸው ፉክክርም ትኩረትን ስቧል። እንግሊዝ የማሸነፊያ የቅድሚያ ግምቱን አግኝታለች። ባልተጠበቀ ሁኔታ ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀለችው ኖርዌይ፣ ያለ ጫና መጫወቷ አሸንፋ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ልታልፍ የምትችልበትን እድል ይፈጥርላታል። የዛሬ ጨዋታ አሸናፊዎች በግማሽ ፍጻሜው ይገናኛሉ።
ስፔን ለግማሽ ፍጻሜ አለፈች
Jul 10, 2026 830
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ሁለተኛ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ስፔን ቤልጂየምን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ማምሻውን በሎስ አንጀለስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፋቢያን ሩዊዝ ስፔንን መሪ ያደረገችውን በ30ኛ ደቂቃ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጎሉ በጥሩ የኳስ ቅብብል የተገኘ ነበር። ቻርልስ ዲ ኬቴላር በ41ኛው ደቂቃ በግንባሩ በመግጨት ያስቆጠረው ጎል ቤልጂየምን አቻ አድርጓል። ዲ ኬቴላር በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ሶስት አድርሷል። ተቀይሮ የገባው ሜኬል ሜሪኖ በ88ኛው ደቂቃ የአሸናፊነቷን ጎል ለስፔን አስቆጥሯል። የ30 ዓመቱ ሜሪኖ 16 ውስጥ ስፔን ፖርቹጋልን ስታሸንፍ ተቀይሮ በመግባት ግብ በማስቆጠር ስፔንን አሸናፊ ማድረጉ የሚታወስ ነው። ተጫዋቹ ምርጥ ተቀያሪነቱን በሁለቱ ጨዋታዎች ላይ አሳይቷል። ስፔን በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ለመጀመሪያ ጊዜ ግብ አስተናግዳለች። የ29 ዓመቱ የስፔን ግብ ጠባቂ ኡናይ ሲሞን በዓለም ዋንጫው ከ649 ደቂቃዎች በኋላ ግብ ተቆጥሮበታል። ሲሞን በውድድሩ ላይ ለረጅም ሰዓታት ግብ ሳይቆጠርበት የቆየ ግብ ጠባቂ በመሆን አዲስ ክብረ ወሰን ሰብሯል። ስፔን በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እድሎችን በመፍጠር ተሽላ ተገኝታለች። የቤልጂየም የአጨዋወት ስልት መከላከል እና በመልሶ ማጥቃት ላይ ያተኮረ ነበር። የአማዱ ኦናና እና ዩሪ ቲሊማንስ በጉዳት ምክንያት አለመሰለፍ የቤልጂየምን የአማካይ ክፍል አሳስቶታል። የ34 ዓመቱ የቤልጂየም ግብ ጠባቂ ቲቦ ኮርቶዋ በጉዳት ምክንያት 71ኛው ደቂቃ ተቀይሮ ወጥቷል። ውጤቱን ተከትሎ ስፔን ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። ለሶስተኛ ጊዜ አራት ውስጥ ገብታለች። ስፔን ለዋንጫ ለማለፍ ከፈረንሳይ ጋር የምታደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ቤልጂየም በዓለም ዋንጫው ለሶስተኛ ጊዜ ወደ ግማሽ ፍጻሜ የማለፍ ህልሟ ሳይሳካ ቀርቷል።
የአውሮፓ ኃያላን ፍጥጫ፤  የስፔንና የቤልጂየም ተጠባቂ የዓለም ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ  ጨዋታ
Jul 10, 2026 939
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- 23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ስፔን ከቤልጂየም ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በሎስ አንጀለስ ስታዲየም ይካሄዳል። ስፔን በ16ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ፖርቹጋልን 1 ለ 0 አሸንፋለች። የአንድ ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ስፔን በዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ታሪኳ ለሰባተኛ ጊዜ ለሩብ ፍጻሜ አልፋለች። ተጋጣሚዋ ቤልጂየም ከአዘጋጅ ሀገራት መካከል አንዷ የሆነችውን አሜሪካን 4 ለ 1 በመርታት ለአራተኛ ጊዜ ወደ ሩብ ፍጻሜ መግባት ችላለች። ሁለት ሀገራት በዓለም ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። ሜክሲኮ እ.አ.አ በ1986 ባዘጋጀችው 13ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በሩብ ፍጻሜው ተገናኝተው ቤልጂየም በመለያ ምት 5 ለ 4 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፋለች። እ.አ.አ በ1990 በጣልያን በተካሄደው 14ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በምድብ አምስት ተገናኝተው ስፔን ቤልጂየምን 2 ለ 1 አሸንፋለች። ሁለቱ ሀገራት ከ36 ዓመታት በኋላ በዓለም ዋንጫው መድረክ ተገናኝተዋል። ሀገራቱ በውድድሮች እና በወዳጅነት ጨዋታዎች 23 ጊዜ ተገናኝተው ስፔን 12 ጊዜ ድል ሲቀናት ቤልጂየም በአምስት ጨዋታዎች አሸንፋለች። በቀሪ ስድስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ስፔን በ23ቱ ጨዋታዎች ላይ 46 ጎሎችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ ቤልጂየም 22 ግቦችን አስቆጥራለች። የ29 ዓመቱ አጥቂ ሚኬል ኦያርዛባል ሁለት ግቦችን በማስቆጠር የስፔን የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ነው። የ33 ዓመቱ የፊት መስመር ተሰላፊ ሮሜሎ ሉካኩ ለቤልጂየም በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ሶስት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሊያንድሮ ትሮሳርድ እና ቻርልስ ደ ኬቴላሬ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን አስቆጥረዋል። በፊፋ የዓለም ሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ ስፔን 3ኛ፣ ቤልጂየም ደግሞ 8ኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ። ላሚን ያማል እና ሮድሪ ከስፔን፣ ኬቨን ደ ብሮይን እና ሮሜሎ ሉካኩ ከቤልጂየም በጨዋታው ልዩነት ይፈጥራሉ ተብለው የሚጠበቁ ናቸው። ሁለቱ የአውሮፓ ኃያላን ሀገራት በዛሬው ጨዋታ አዝናኝ እና ማጥቃት ላይ የተመሰረተ የጨዋታ እንቅሰቃሴ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። የዛሬው ጨዋታ አሸናፊ በግማሽ ፍጻሜው ከፈረንሳይ ጋር ይጫወታል። ፈረንሳይ ትናንት ሞሮኮን 2 ለ 0 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅላለች።
ፈረንሳይ ሞሮኮን በመርታት ለግማሽ ፍጻሜ አለፈች
Jul 9, 2026 1163
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ ማለፍ መርሐ ግብር ፈረንሳይ ሞሮኮን 2 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በቦስተን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኪሊያን ምባፔ በ60ኛው እና ኡስማን ዴምቤሌ በ65ኛው ደቂቃ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ምባፔ በ28ኛው ደቂቃ ፍጹም ቅጣት ምት ስቷል። ፈረንሳይ በጨዋታው ፍጹም ብልጫ ወስዳለች። የተደራጀ መከላከል እና የመልሶ ማጥቃት የአጨዋወት ስልት የተከተለችው ሞሮኮ ግልጽ የግብ እድሎችን መፍጠር ተስኗታል። የ27 ዓመቱ ኪሊያን ምባፔ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ስምንት በማድረስ ከአርጀንቲናው ሊዮኔል ሜሲ ጋር በጎል እኩል በመሆን ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል ብልጫ ወስዶ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ይገኛል። በአጠቃላይ በውድድሩ ላይ 20 ጎሎች ከመረብ ላይ በማሳረፍ በምንጊዜም ከፍተኛ አስቆጣሪነቱ ከሜሲ (21 ጎል) በአንድ አንሶ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ምባፔ በዓለም ዋንጫው የጥሎ ማለፍ ምዕራፍ 12ኛ ጎሉን በማስቆጠር በውድድሩ አዲስ ክብረ ወሰን አስመዝግቧል። ለብሔራዊ ቡድኑ 64ኛ ጎሉን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ምባፔ በ77ኛው ደቂቃ ጉዳት አጋጥሞት ተቀይሮ ወጥቷል። የባለንዶር ባለቤቱ ኡስማን ዴምቤሌ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ አምስተኛ ጎሉን አስቆጥሯል። ውጤቱን ተከትሎ ፈረንሳይ ግማሽ ፍጻሜውን የተቀላቀለች የመጀመሪያዋ ሀገር ሆናለች። በዓለም ዋንጫው ለግማሽ ፍጻሜ ስታልፍ የአሁኑ ለሰባተኛ ጊዜ ነው። ፈረንሳይ በግማሽ ፍጻሜው ከስፔን እና ቤልጂየም አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ሞሮኮ የዓለም ዋንጫ ጉዟዋ ሩብ ፍጻሜው ላይ አብቅቷል። ለተከታታይ ዓለም ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ የመግባት ህልሟ ሳይሳካ ቀርቷል። በሩብ ፍጻሜው ላይ አፍሪካን የወከለችው ብቸኛ ሀገር ሞሮኮ ከውድድሩ ተሰናብታለች። የሰሜን አፍሪካዋ ሀገር ከተሳተፉ 10 ቡድኖች መካከል የተሻለ ርቀት መጓዝ ችላለች። ሞሮኮ በ22ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ የደረሰች የመጀመሪያዋ የአፍሪካ ሀገር መሆኗ የሚታወስ ነው። በዘንድሮ የዓለም ዋንጫ አፍሪካ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ 10 ሀገራት አሳትፋለች።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ዋንጫን በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ አነሳ
Jul 9, 2026 773
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2 /2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የፍጻሜ ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ሲዳማ ቡናን 2 ለ 0 አሸንፏል። ረፋድ ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጋናዊው አጥቂ ኮንኮኒ ሃፊዝ በ47ኛው እና በየነ ባንጃ በ99ኛው ደቂቃ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጨዋታውን በርካታ ደጋፊዎች በስታዲየም በመገኘት ተከታትለውታል። ውጤቱን ተከትሎ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የኢትዮጵያ ዋንጫን አንስቷል። በዘንድሮው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ በ46 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዞ ላጠናቀቀው ወልዋሎ የዛሬው ድል ትልቅ ትርጉም የሚሰጠው ነው። የኢትዮጵያ ዋንጫ ድሉ በ1948 ዓ.ም ለተመሰረተው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ትልቅ ከሚባሉ ስኬቶች መካከል የሚጠቀስ ነው። ሲዳማ ቡና በአህጉራዊ ውድድር ተሳትፎውን በማረጋገጡ ምክንያት፣ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የውድድር ደንብ መሰረት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የፍጻሜ ተፋላሚ መሆኑን ተከትሎ የጨዋታውን ውጤት ሳይጠብቅ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ላይ ኢትዮጵያን ወክሎ በቀጣዩ ዓመት መሳተፉን ማረጋገጡ የሚታወስ ነው። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና ለተከታታይ ዓመት ለኢትዮጵያ ዋንጫ ቢደርስም ዋንጫውን ለመጀመሪያ ጊዜ የማሸነፍ ህልሙን ማሳከት አልቻለም። የዘንድሮው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አሸናፊ ሲዳማ ቡና፣ ዓመቱን በሁለት ዋንጫ የማጠናቀቅ ፍላጎቱ ሳይሳካ ቀርቷል። ሲዳማ ቡና ፕሪሚየር ሊጉን ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ያነሳ ሲሆን ይህን ተከትሎም በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ መሳተፉን አረጋግጧል። ሁለቱ ቡድኖች በቀጣዩ ዓመት ኢትዮጵያን በአህጉራዊ የክለብ ውድድሮች ላይ ወክለው ይሳተፋሉ። በ1937 ዓ.ም የተጀመረው የኢትዮጵያ ዋንጫ የ80 ዓመት ታሪክ ያለው አንጋፋ ውድድር ነው።
በክልሉ በአካል ብቃት እንቅስቃሴ ጤናማና አምራች ዜጋን የማፍራት ሥራው ይጠናከራል
Jul 9, 2026 596
ሆሳዕና፤ ሐምሌ 2/2018 (ኢዜአ)፦በማዕክላዊ ኢትዮጵያ ክልል የአካል ብቃት እንቅስቃሴን ባህል በማድረግ ጤናማና አምራች ዜጋን ለማፍራትና አብሮነትን ለማሳድግ የተጀመረው ሥራ እንደሚጠናከር የክልሉ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ገለጸ። የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እንዲሁም የወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ሠራተኞችና ሃላፊዎች የተሳተፉበት የአካል ብቃት እንቅስቃሴ መርሀግብር ዛሬ በሆሳዕና ከተማ ተካሂዷል።   የክልሉ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ሀላፊ አቶ ጌታቸው ሌሊሾ በዚህ ወቅት እንዳሉት በክልሉ የአካል ብቃት እንቅስቃሴን ባህል በማድረግ ጤናማና አምራች ዜጋን ለማፍራትና የአብሮነት እሴትን ለማጠናከር እየተሰራ ነው። በየአካባቢው የሚካሄደው የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ጤናማና አምራች ዜጋ ለማፍራት ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ገልጸው፣ የእርስ በርስ ግንኙነትን በማሳደግ በኩል ፋይዳው የጎላ በመሆኑም ስፖርቱን ለማስቀጠል ይሰራል ብለዋል። የዛሬው መርሀግብር ስፖርትን ባህል የማድረግ ሥራን ከማጠናከር ባለፈ ወጣቶች በበጎ ፍቃድ ሥራ እንዲሳተፉ ያለመ እንደሆነና መሰል መርሀግብሮችም በየአካባቢው እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   የቢሮው ምክትል ሀላፊና የስፖርት ዘርፍ ሀላፊ አቶ ሰይፈ አለሙ በበኩላቸው እንደገለጹት በስፖርት ልማት ዘርፉ ክልሉ ያለውን አቅም ለይቶ መጠቀም የሚያስችል ሥራ እየተሰራ ነው። ለእዚህም ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ማዘወተሪያ ስፍራዎችን ለማስፋትና በሁሉም የስፖርት ዘርፍ ታዳጊና ተተኪ ስፖርተኞችን በማፍራት የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን አመልክተዋል። በተያዘው ክረምት ክልሉን የሚወክል የሰርከስ ቡድን ለማቋቋም መታቀዱን የገለጹት ሀላፊው የአካል ብቃት እንቅስቃሴዎችም ብቃት ያላቸው ወጣቶችን ለመለየት አይነተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። በአካል ብቃት እንቅስቃሴ ከተሳተፉት የማህበረሰብ ክፍሎች መካከል አቶ ብዙአየሁ ሀይሌ እና አቶ አብድልፈታ ናስር ጤናቸውን ለመጠበቅና የተሟላ ስብዕና ለመገንባት በአካል ብቃት እንቅስቃሴ በመርሀግብሩ ላይ መሳተፋቸውን ተናግረዋል። ስፖርቱ በተለይ የእርስ በርስ ግንኙነታቸውን ከማጠናከር ባለፈ የበጎ ፈቃድ ስራዎችን በጋራ ለማከናወን ምቹ ሁኔታ እንደተፈጠረላቸውም ገልጸዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ ከተለያዩ መዋቅሮች የተውጣጡ ስፖርተኞችም መሳተፋቸው ታውቋል።        
ፈረንሳይ ከሞሮኮ፦ ማን ወደ ግማሽ ፍፃሜው ያልፋል?
Jul 9, 2026 683
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2018 (ኢዜአ)፦ የ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ ከእንድ ቀን እረፍት በኋላ ዛሬ በሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ይመለሳል። ምሽት አምስት ላይ ፈረንሳይ ከሞሮኮ በቦስተን ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። ፈረንሳይ በ16ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ፓራጓይን በመርታት በዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ታሪኳ ለ10ኛ ጊዜ ወደ ሩብ ፍጻሜው ገብታለች። ተጋጣሚዋ ሞሮኮ ከዓለም ዋንጫው አዘጋጅ ሀገራት መካከል አንዷ የሆነችውን ካናዳን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ሞሮኮ በዓለም ዋንጫው ታሪክ ሁለት ጊዜ ሩብ ፍጻሜ የገባች የመጀመሪያዋ ሀገር ሆናለች። ሁለቱ ቡድኖች ከዚህ ቀደም በዓለም ዋንጫው አንድ ጊዜ ተገናኝተዋል። ኳታር እ.አ.አ በ2022 ባዘጋጀችው 22ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በግማሽ ፍጻሜው ተገናኝተው ፈረንሳይ 2 ለ 0 አሸንፋለች። ቴዎ ሄርናንዴዝ እና ራንዳል ኮሎ ሙዋኒ በወቅቱ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። ሞሮኮ በጨዋታው ሽንፈት ቢገጥማትም በዓለም ዋንጫ ታሪክ ግማሽ ፍጻሜ የገባች የመጀመሪያ ሀገር በመሆን ታሪክ ሰርታለች። ሁለቱ ሀገራት በአጠቃላይ በውድድር እና በወዳጅነት ጨዋታዎች ላይ ስድስት ጊዜ ተገናኝተዋል። ፈረንሳይ አራት ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዛለች። ሞሮኮ አንድ ጊዜ ስታሸንፍ በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። ሞሮኮ በታሪኳ ፈረንሳይን ማሸነፍ የቻለችው አንድ ጊዜ ብቻ ሲሆን እሱም እ.ኤ.አ. በ1998 በንጉሥ ሀሰን ሁለተኛ ዋንጫ ላይ ሁለት እኩል ተለያይተው በፍጹም ቅጣት ምት 6 ለ 5 ያሸነፈችበት ጨዋታ ነበር። በነዚህ ስድስት ጨዋታዎች ላይ ፈረንሳይ 14 ጎሎችን ስታስቆጥር፣ ሞሮኮ 7 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፋለች። የዓለም ዋንጫውን ታነሳለች ተብላ ሰፊ ግምት ያገኘችው ፈረንሳይ የማጥቃት ኃይሏ ለተጋጣሚዎቿ የራስ ምታት ሆኗል። የ27 ዓመቱ ኪሊያን እምባፔ በዘንድሮው ውድድር 7 ግቦችን በማስቆጠር እና ሁለት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል ተመሳሳይ የግብ መጠን ያለውን አርጀንቲናዊውን ሊዮኔል ሜሲ በመብለጥ የኮከብ ግብ አግቢነቱን እየመራ ይገኛል። ምባፔ በዓለም ዋንጫው በአጠቃላይ 19 ግቦችን ከመረብ ላይ ያሳረፈ ሲሆን ከምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪው ሜሲ (20 ጎሎች) በአንድ ግብ ዝቅ ብሎ ይገኛል። ማይክል ኦሊሴ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ አምስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል ድንቅ ብቃቱን እያሳየ ይገኛል። በሞሮኮ በኩል ሶስት ግቦችን በዓለም ዋንጫው ያስቆጠረው የ25 ዓመቱ አጥቂ ኢስማኤል ሳይባሪ ከካናዳ ጋር በነበረው ጨዋታ ባጋጠመው የጡንቻ መሳሳብ ጉዳት ከዛሬው ጨዋታ ውጪ ሆኗል። የሳይባሪን ቦታ ሶፊያን ራሂሚ በዛሬው ጨዋታ እንደሚሸፍን ይጠበቃል። በዓለም ዋንጫው በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን ያስቆጠሩት አዜዲን ኡናሂ እና ሶፊያን ራሂሚ የማጥቃት እንቅስቃሴውን በዋነኛነት ይመሩታል። ምርጥ ጓደኛማቾች እየተባሉ የሚጠሩት አሽራፍ ሀኪሚና ኪሊያን እምባፔ በጨዋታው ላይ የሚኖራቸው ፉክክር ተጠባቂ ሆኗል። ፈረንሳንይ ጨዋታውን የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት ብትወስድም ሞሮኮ ጠንካራ ተፋላሚነቷን ታሳያለች ተብሎ ይጠበቃል። የዛሬው ጨዋታ አሸናፊ በግማሽ ፍጻሜው ከስፔን እና ቤልጂየም አሸናፊ ጋር ይገናኛል።
የኢትዮጵያ ዋንጫን ማን ያነሳል?  ሲዳማ ቡና ወይስ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ?
Jul 9, 2026 499
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2 /2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የፍጻሜ ጨዋታ በሲዳማ ቡና እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ መካከል ዛሬ ይደረጋል። ጨዋታው ከረፋዱ አምስት ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል። በግማሽ ፍጻሜው ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ መድንን፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ መቀሌ 70 እንደርታን በተመሳሳይ በመለያ ምት አሸንፈዋል። ሲዳማ ቡና ለሁለተኛ ተከታታይ ዓመት ለኢትዮጵያ ዋንጫ ፍጻሜ ደርሷል። ቡድኑ ባለፈው ዓመት ውድድሩን አሸንፎ የነበረ ቢሆንም ቅጣት የተጣለባቸውን ተጫዋቾችን በፍጻሜው ላይ በመጠቀሙ ምክንያት ዋንጫው ለወላይታ ድቻ መሰጠቱ የሚታወስ ነው። ሲዳማ ቡና ለመጀመሪያ ጊዜ የኢትዮጵያ ዋንጫ ለማንሳት ይፋለማል። ተጋጣሚው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ለኢትዮጵያ ዋንጫ ፍጻሜ ሲያልፍ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ሁለቱ ክለቦች በዘንድሮው የውድድር ዓመት ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። በሊጉ ባደረጓቸው ሁለት ጨዋታዎች ሲዳማ ቡና አንድ ጊዜ ሲያሸንፍ በቀሪው መርሐ ግብር አቻ ተለያይተዋል። ቡድኖቹ በሊጉ የመጀመሪያ ሳምንት ተገናኝተው ሲዳማ ቡና 4 ለ 1 ማሸነፉ አይዘነጋም። በወቅቱ በነበረው ጨዋታ አበባው አጂሶ፣ አስቻለው ሙሴ፣ ተመስገን መንገሻ እና የወልዋሎው ጌታሁን ባፋ በራሱ ላይ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሰመረ ሀፍታይ ለወልዋሎ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ጋር አገናኝቷል። በ20ኛ ሳምንት ባደረጉት ጨዋታ ደግሞ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ሲዳማ ቡና የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ያነሳ ሲሆን ይህን ተከትሎም በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ መሰታፉን አረጋግጧል። ቡድኑ የውድድር ዓመቱን በሁለት ዋንጫ ለመደምደም ዛሬ ወደ ሜዳ ይገባል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የዘንድሮውን የውድድር ዓመት በ46 ነጥብ 16ኛ ደረጃን በመያዝ አጠናቋል። ሲዳማ ቡና በአህጉራዊ ውድድር ተሳትፎውን በማረጋገጡ ምክንያት፣ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የውድድር ደንብ መሰረት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ የፍጻሜ ተፋላሚ መሆኑን ተከትሎ የጨዋታውን ውጤት ሳይጠብቅ በቀጥታ በካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ላይ መሳተፉን አረጋግጧል። ሁለቱም ቡድኖች ታሪካዊውን የኢትዮጵያ ዋንጫ ለማንሳት ይፈለማሉ። በ1937 ዓ.ም የተጀመረው የኢትዮጵያ ዋንጫ የ80 ዓመት ታሪክ ያለው አንጋፋ ውድድር ነው።
ስዊዘርላንድ ከ72 ዓመታት በኋላ ለዓለም ዋንጫ ሩብ ፍጻሜ አለፈች
Jul 8, 2026 922
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/ 2018 (ኢዜአ):- በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የ16ቱ የጥሎ የመጨረሻ ማለፍ መርሐ ግብር ስዊዘርላንድ ኮሎምቢያን በመለያ ምት አሸንፋለች። ማምሻውን በቢሲ ፔሌስ ቫንኩቨር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በመደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ይህንንም ተከትሎ 30 ደቂቃ የተጨመረ ሲሆን ግብ ባለመቆጠሩ ምክንያት ወደ መለያ ምት አምርቷል። በዚህም ስዊዘርላንድ 4 ለ 3 በማሸነፍ ወደ ሩብ ፍጻሜው ገብታለች። ስዊዘርላንድ ከ72 ዓመታት በኋላ ለሩብ ፍጻሜ አልፋለች። በታሪኳ ለአራተኛ ጊዜ ስምንት ውስጥ ገብታለች። በሩብ ፍጻሜው ከአርጀንቲና ጋር ትጫወታለች። የደቡብ አሜሪካዋ ኮሎምቢያ በዓለም ዋንጫ ለሁለተኛ ጊዜ ለሩብ ፍጻሜ የማለፍ ህልሟ አልተሳካም። አጠቃላይ የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ሳቢ ያልነበረ እና የግብ እድሎች በበቂ ሁኔታ ያልተፈጠሩበት ነበር። ጨዋታውን ተከትሎ የ16ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ተጠናቋል። የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ከአንድ ቀን እረፍት በኋላ ከሐምሌ 2 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳሉ። ፈረንሳይ ከሞሮኮ፣ ኖርዌይ ከብራዚል፣ ስፔን ከቤልጂየም እና አርጀንቲና ከስዊዘርላንድ በሩብ ፍጻሜው የሚደረጉ ጨዋታዎች ናቸው።
የወቅቱ የዓለም ዋንጫ ባለቤት አርጀንቲና ግብጽን በማሸነፍ ለሩብ ፍጻሜ አለፈች
Jul 7, 2026 851
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018 (ኢዜአ)፦ የ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የ16ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ አርጀንቲና ግብጽን ከ2 ለ 0 ከመመራት ተነስታ 3 ለ 2 አሸንፋለች። ማምሻውን በአትላንታ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ያስር ኢብራሂም በ15ኛው እና ሙስጠፋ ዚኮ በ67ኛው ደቂቃ ለግብጽ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሙስጠፋ ዚኮ በ58ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል በቪዲዮ የታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ጥፋት በመሰራቱ ተሽሯል። ክርስቲያን ሮሜሮ በ79ኛው፣ ሊዮኔል ሜሲ በ83ኛው እና ኤንዞ ፈርናንዴዝ በ93ኛው ደቂቃ የአርጀንቲናን ግቦች አስቆጥረዋል። በጨዋታው የግብጹ ግብ ጠባቂ ሙስጠፋ ሾቤር ያለቀላቸው ግቦችን በማዳን ድንቅ ብቃቱን አሳይቷል። አርጀንቲና ከውድድሩ ከመሰናበት ጫፍ ደርሳ ውጤቱን በመቀልበስ ወደ ሩብ ፍጻሜው ገብታለች። ግብጽ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ ሩብ ፍጻሜ የመግባት ህልሟ ሳይሳካ ቀርቷል። የ2 ለ 0 ውጤቷንም ማስጠበቅ አልቻለችም። ሊዮኔል ሜሲ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ስምንት በማድረስ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን አጠናክሯል። በዓለም ዋንጫው በአጠቃላይ ያገባቸውን ጎሎች ብዛት 21 በማድረስ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን አጠናክሯል። ሜሲ በዘጠኝ ተከታታይ የዓለም ዋንጫዎች ላይ ግብ ያስቆጠረ እና በውድድሩ ዘጠኝ ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ ያቀበለ የመጀመሪያ ተጫዋች ሆኗል። ለሀገሩም 126ኛውን ግብ ከመረብ ላይ ያሳረፈ ሲሆን በፕሮፌሽናል የእግር ኳስ ተጫዋችነት ዘመኑ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት 918 አድርሷል። የ39 ዓመቱ አርጀንቲናዊ በ21ኛው ደቂቃ ፍጹም ቅጣት ስቷል። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ የሳታቸውን ፍጹም ቅጣት ምቶች ብዛት ሁለት ደርሰዋል። ሜሲ በአንድ ዓለም ዋንጫ ሁለት ፍጹም ቅጣት ምት የሳተ የመጀመሪያው ተጫዋች ሆኗል። በአጠቃላይ በተሳተፋባቸው ዓለም ዋንጫዎች ላይ አራት ፍጹም ቅጣት ምቶችን ወደ ግብ መቀየር አልቻለም። አርጀንቲና በሩብ ፍጻሜው ከኮሎምቢያ እና ስዊዘርላንድ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ኮሎምቢያ እና ስዊዘርላንድ ምሽት አምስት ሰዓት ላይ በቢሲ ፕሌስ ቫንኩቨር ስታዲየም ይጫወታሉ።
ወደ ሩብ ፍጻሜ ለመድረስ የሚደረጉ ተጠባቂ ፍልሚያዎች፦ አርጀንቲና ከግብፅ፤ ስዊዘርላንድ ከኮሎምቢያ
Jul 7, 2026 711
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30 /2018 (ኢዜአ)፦ የ23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ የ16ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። ምሽት አንድ ሰዓት ላይ አርጀንቲና ከግብጽ በአትላንታ ስታዲየም ይጫወታሉ። አርጀንቲና በ32ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ኬፕቨርዴን 3 ለ 2 አሸንፋለች። የወቅቱ የዓለም ዋንጫ ባለቤት ከተጋጣሚዋ የበረታ ፉክክር ቢገጥማትም፣ ድል ቀንቷት ወደ ቀጣዩ ዙር ተሸጋግራለች። አርጀንቲና በውድድሩ የተሳትፎ ታሪኳ ለ10ኛ ጊዜ ወደ 16ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር አልፋለች። ከዚህ በነበራት የዘጠኝ ጊዜ ተሳትፎ ሰባቱን በማሸነፍ ወደ ሩብ ፍጻሜ ስታልፍ በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ተሸንፋለች። ተጋጣሚዋ ግብጽ ከአውስትራሊያ ጋር አንድ አቻ በመለያየት በመለያ ምት የ4 ለ 2 ድል በማስመዝገብ በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ 16 ውስጥ ገብታለች። የሰሜን አፍሪካዋ ሀገር በጥሎ ማለፍ ስታሸንፍ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። አርጀንቲና እና ግብጽ ከዚህ ቀደም በዓለም ዋንጫው ተገናኝተው አያውቁም። እ.አ.አ በ2008 በካይሮ ኢንተርናሽናል ስታዲየም ባደረጉት የወዳጅነት ጨዋታ አርጀንቲና 2 ለ 0 አሸንፋለች። ሰርጂዮ አጉዌሮ እና ኒኮላስ ቡርዲሶ በወቅቱ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ሰባት ጎሎችን ያስቆጠረው እና በ20 ጎሎች የውድድሩ የምንጊዜም ግብ አስቆጣሪ ሊዮኔል ሜሲ በጨዋታው የሚጠበቅ ተጫዋች ነው። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ሰባት ጎሎችን ያስቆጠረውና በ20 ጎሎች የውድድሩ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ የሆነው ሊዮኔል ሜሲ፣ በጨዋታው ከፍተኛ ግምት የተሰጠው ተጫዋች ነው። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ሁለት ጎሎችን ያስቆጠረው ኢማም አሹር እና አምበሉ መሐመድ ሳላህ በግብጽ በኩል የሚጠበቁ ተጫዋቾች ናቸው። የጨዋታው አሸናፊ በሩብ ፍጻሜው ከስዊዘርላንድ እና ኮሎምቢያ አሸናፊ ጋር ይገናኛል። ስዊዘርላንድ ከኮሎምቢያ በቢሲ ፕሌስ ቫንኩቨር ስታዲየም ምሽት አምስት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በ32ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ስዊዘርላንድ አልጄሪያን 2 ለ 0 አሸንፋለች። ይህም ከ88 ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ያስመዘገበችው የጥሎ ማለፍ ድል ነው። ተጋጣሚዋ ኮሎምቢያ ጋናን 1 ለ 0 በመርታት 16 ውስጥ ገብታለች። የደቡብ አሜሪካዋ ሀገር በዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ታሪኳ ለአራተኛ ጊዜ በጥሎ ማለፉ ትጫወታለች። ሁለቱ ሀገራት በዓለም ዋንጫው ከዚህ ቀደም አንድ ጊዜ ተገናኝተዋል። አሜሪካ እ.አ.አ በ1994 ባዘጋጀችው 15ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው ኮሎምቢያ 2 ለ 0 አሸንፋለች። ሄርናን ጋቪሪያ እና ሃሮልድ ሎዛኖ ግቦቹን በወቅቱ ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። ሀገራቱ ከ32 ዓመታት በኋላ በጥሎ ማለፍ ምዕራፍ ተገናኝተዋል። ቡድኖቹ በአጠቃላይ ሶስት ጊዜ ተገናኝተው ኮሎምቢያ በሁለቱ ድል ሲቀናት በቀሪው አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። የስዊዘርላንድ እና ኮሎምቢያ ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። የዛሬ ጨዋታ አሸናፊዎች በሩብ ፍጻሜው ይገናኛሉ። ሞሮኮ፣ ፈረንሳይ፣ ኖርዌይ፣ እንግሊዝ፣ ስፔን እና ቤልጂየም እስከ አሁን ሩብ ፍጻሜ የገቡ ሀገራት ናቸው።
ቤልጂየም አሜሪካን በመርታት ሩብ ፍጻሜ ገብታለች
Jul 7, 2026 590
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/ 2018 (ኢዜአ):- በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የ16ቱ የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ቤልጂየም አሜሪካን 4 ለ 1 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፋለች። ከእኩለ ሌሊት በኋላ በሲያትል ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ቻርልስ ደ ኬቴላሬ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሃንስ ቫንከን እና ሮሜሎ ሉካኩ ቀሪዎቹን ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ማሊክ ቲልማን የአሜሪካን ብቸኛ ግብ አስቆጥሯል። አጥቂው ሮሜሎ ሉካኩ በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ሶስት አድርሷል። በአጠቃላይ ደግሞ በውድድሩ ላይ ከመረብ ላይ ያሳረፋቸውን ጎሎች ወደ ስምንት ከፍ አድርጓል። ለቤልጂየም ብሔራዊ ቡድንም 93ኛ ግቡን አስቆጥሯል። በጨዋታው ቤልጂየም ከፍተኛ ብልጫ ወስዳለች። የተመለከተው ቀይ ካርድ በአነጋጋሪ ሁኔታ የተነሳለት የአሜሪካው አጥቂ ፍሎሪያን ባሎጉን በጨዋታው ላይ ተሰልፏል። ውጤቱን ተከትሎ ቤልጂየም ወደ ሩብ ፍጻሜ የገባች ሲሆን ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ ከስፔን ጋር ትፋለማለች። ከዘንድሮ የዓለም ዋንጫ አዘጋጅ ሀገራት መካከል አንዷ የሆነችው አሜሪካ የውድድሩ ጉዟዋ 16 ውስጥ ተገቷል። አሜሪካ ከ24 ዓመታት በኋላ ወደ ዓለም ዋንጫው ሩብ ፍጻሜ የመግባት ህልሟ ሳይሳካ ቀርቷል። ጣምራ አዘጋጅ የሆኑት አሜሪካ፣ ካናዳ እና ሜክሲኮ በ16ቱ ዙር የጥሎ ማለፍ መርሐ ግብር ከውድድሩ ተሰናብተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም