ቀጥታ፡
ስፖርት
የአፍሪካ ዋንጫን ለበርካታ ጊዜ ያዘጋጁ ሀገራት
Jan 4, 2026 80
የአፍሪካ ዋንጫ ከተጀመረ 68 ዓመታትን አስቆጥሯል። እ.አ.አ በ1957 የተካሄደውን የመጀመሪያውን የአፍሪካ ዋንጫ ያዘጋጀችው የምስራቅ አፍሪካዊቷ ሀገር ሱዳን ናት። በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ 19 ሀገራት ውድድሩን ለብቻ ወይም በጣምራ አዘጋጅተዋል። ግብጽ የአፍሪካ ዋንጫን አምስት ጊዜ በማስተናገድ ቀዳሚውን ስፍራ ይዛለች። ካዘጋጀቻቸው ውድድሮች መካከል ሶስቱን በሀገሯ አስቀርታለች። የምዕራብ አፍሪካዊቷ ሀገር ጋና አራት ጊዜ ውድድሩን በማዘጋጀት ሁለተኛ ደረጃ ላይ ስትቀመጥ ከዚህ ውስጥ በአንድ አጋጣሚ ዋንጫውን አንስታለች። ኢትዮጵያ እና ቱኒዚያ በተመሳሳይ ሶስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አዘጋጅተዋል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1962 ባዘጋጀችው ሶስተኛ የአፍሪካ ዋንጫ ግብጽን በፍጻሜው 4 ለ 2 በመርታት ብቸኛ ዋንጫውን አንስታለች። እ.አ.አ በ1968 ባዘጋጀችው ስድስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ዋንጫውን አንስታለች። ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን ያዘጋጀችው እ.አ.አ በ1976 10ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ሲሆን በፍጻሜው ሞሮኮ ጊኒን በማሸነፍ ዋንጫውን አንስታለች። ሞሮኮ፣ ካሜሮን፣ ሱዳን፣ ኮትዲቯር፣ ጋቦን፣ ደቡብ አፍሪካ እና ኢኳቶሪያል ጊኒ በተመሳሳይ ሁለት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አዘጋጅተዋል። የዘንድሮውን ጨምሮ ከ35ቱ የአፍሪካ ዋንጫዎች መካከል ሁለቱ ብቻ ናቸው በጣምራ የተዘጋጁት። ሞሮኮ እ.አ.አ 1988 ካዘጋጀችው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በኋላ ውድድሩን በድጋሚ የማስተናገድ እድል ተሰጥቷታል። እ.አ.አ በ2027 የሚካሄደውን 36ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ዩጋንዳ፣ ኬንያ እና ታንዛንያ በጣምራ ያዘጋጃሉ። ይህም ሀገራቱ ውድድሩን ለመጀመሪያ ጊዜ በጋራ የማዘጋጀት እድል ሰጥቷቸዋል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2029 የሚካሄደውን 37ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት ጥያቄ ማቅረቧ ይታወቃል።
ማንችስተር ሲቲ ከቼልሲ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው 
Jan 4, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018 (ኢዜአ):- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ስድስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ ማንችስተር ሲቲ ከቼልሲ በኢትሃድ ስታዲየም ይጫወታሉ። ማንችስተር ሲቲ በ41 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቼልሲ በ30 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ ሲገናኙ የአሁኑ ለ57ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 56 ጨዋታዎች ቼልሲ 27 ጊዜ ሲያሸንፍ፣ ማንችስተር ሲቲ 20 ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ ዘጠኝ ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች በነበራቸው የእርስ በእርስ ግንኙነት ማንችስተር ሲቲ ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ሁለት ጊዜ ነጥብ ተጋርተዋል። ማንችስተር ሲቲ በ19ኛ ሳምንት ከሰንደርላንድ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል።   ከአሰልጣኝ ኢንዞ ማሬስካ ጋር የተለያየው ቼልሲ በበኩሉ ባለፉት ሶስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ማንችስተር ሲቲ ካሸነፈ ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት መልሶ ወደ አራት ዝቅ ያደርጋል። ቼልሲ ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። የ40 ዓመቱ ማይክል ኦሊቨር ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች መርሃ ግብሮች ሊድስ ዩናይትድ ከማንችስተር ዩናይትድ ከቀኑ 9 ሰዓት ከ30 እና ፉልሃም ከሊቨርፑል ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቶተንሃም ሆትስፐርስ ከሰንደርላንድ፣ ኤቨርተን ከብሬንትፎርድ እና ኒውካስትል ዩናይትድ ከክሪስታል ፓላስ በተመሳሳይ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከሀድያ ሆሳዕና ይጫወታል 
Jan 4, 2026 62
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 26/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ሀድያ ሆሳዕና ከሲዳማ ቡና በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሀድያ ሆሳዕና በሊጉ 12 ጨዋታዎችን አከናውኖ አራት ጊዜ ድል ሲቀናው በተመሳሳይ አራት ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ቡድኑ በ16 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በበኩሉ በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 12 ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ሲያሸንፍ ሽንፈት ያስተናገደው አንድ ጊዜ ብቻ ነው። አራት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። ሲዳማ ቡና በ25 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ሲዳማ ካሸነፈ መሪነቱን ያጠናክራል። ሀድያ ሆሳዕና ድል ከቀናው አራተኛ ተከታታይ የሊግ ድሉን ያስመዘግባል። ነጌሌ አርሲ ከመቻል ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ነጌሌ አርሲ በውድድር ዓመቱ 12 ጨዋታዎችን አድርጎ አምስቱን ሲያሸንፍ በሶስቱ ተሸንፏል። በአራቱ ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ 19 ነጥብ በመሰብሰብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው መቻል በሊጉ ካከናወናቸው 12 ጨዋታዎች መካከል በአራቱ ድል ሲቀዳጅ ሁለት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪዎቹ ስድስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። ቡድኑ በ20 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ጨዋታው ነጌሌ አርሲ በድል ጉዞ ለመቀጠል፣ መቻል ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። ሸገር ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ በ12 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ15 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሸገር ከተማ ከሶስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል ለመመለስ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሃ ግብር ኢትዮጵያ ቡና ከምድረ ገነት ሽሬ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ቡና በ15 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ምድረ ገነት ሽሬ በ14 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ጨዋታው ኢትዮጵያ ቡና ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ፣ ምድረ ገነት ሽሬ ከአራት ተከታታይ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
በጥሎ ማለፉ አዘጋጇ ሞሮኮ ከታንዛንያ ደቡብ አፍሪካ ከካሜሮን የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Jan 4, 2026 74
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። አዘጋጇ ሞሮኮ ከታንዛንያ ምሽት አንድ ሰዓት በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።   ሞሮኮ በምድብ አንድ ሰባት ነጥብ በመሰብሰብ አንደኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። የምስራቅ አፍሪካዋ ታንዛንያ በምድብ ሶስት በሁለት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ ምርጥ ሶስተኛ ሆና ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ሁለቱ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። ኮትዲቯር እ.አ.አ በ2023 ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አራት ተገናኝተው ሞሮኮ ታንዛንያን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ሮማን ሳይስ፣ አዝዲን ኡናሂ እና የሱፍ ኤን-ኔይስሪ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሶስቱም ተጫዎቾች በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ የሞሮኮ ስብስብ ውስጥ ይገኛሉ። ታንዛንያ ወደ ሩብ ለፍጻሜ ለመግባት በአፍሪካ ምርጡ ብሄራዊ ቡድን የሚል ስያሜ ያገኘውን ሞሮኮን የማሸነፍ ጠንካራ ፈተና ይጠብቃታል። በሌላኛው መርሃ ግብር ምሽት አራት ሰዓት ላይ ደቡብ አፍሪካ ከካሜሮን በአል መዲና ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።   ደቡብ አፍሪካ በምድብ ሁለት በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በምድብ ስድስት የነበረችው ካሜሮን በሰባት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቀቅ 16ቱን ተቀላቅላች። ሀገራቱ በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ1996 ባዘጋጀችው 20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው አዘጋጇ ሀገር 3 ለ 0 አሸንፋለች። ፊሊሞን ማሲንጋ፣ ማርክ ዊሊያምስ እና ጆን ሌሲባ ሞሾዩ ግቦችን አስቆጥረዋል። በሁሉም ውድድሮች ባደረጓቸው ስምንት ጨዋታዎች ደቡብ አፍሪካ አምስት ጊዜ ስታሸንፍ አምስት ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። ደቡብ አፍሪካ አንድ ጊዜ፣ ካሜሮን አምስት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አሸንፈዋል። በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ በምድባቸው ጥሩ ብቃት ያሳዩት ሀገራት የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የዛሬ ጨዋታ አሸናፊዎች በሩብ ፍጻሜው የሚጫወቱ ይሆናል። ትናንት በተደረጉ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ሴኔጋል እና ማሊ ለሩብ ፍጻሜ አልፈዋል።
አርሰናል ቦርንማውዝን በማሸነፍ የሊጉን መሪነት አጠናከረ
Jan 3, 2026 103
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 20ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርሰናል ቦርንማውዝን 3 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በቫይታሊቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ዴክላን ራይስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ጋብርኤል ማጋሌሽ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ኢቫኒልሰን እና ጁኒየር ክሩፒ ለቦርንማውዝ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ለኢቫኒልሰን ጎል መቆጠር ትልቅ ስህተት ሰርቶ የነበረው የአርሰናሉ ተከላካይ ጋብርኤል ማጋሌሽ ለመድፈኞቹ ግብ በማስቆጠር ቡድኑን ክሷል። አርሰናል በሁለተኛው አጋማሽ የወሰደው ብልጫ ጨዋታውን እንዲያሸንፍ አስችሎታል። በውድድር ዓመቱ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው የሊጉ መሪ አርሰናል ነጥቡን ወደ 48 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ አስቶንቪላ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ስድስት ከፍ ማድረግ ችሏል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቦርንማውዝ በ23 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቡድኑ የዛሬውን ጨምሮ ባለፉት 11 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።
የዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ የኮከብ ግብ  አግቢነት ፉክክር
Jan 3, 2026 94
  35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። ታህሳስ 12 ቀን 2018 ዓ.ም የተጀመረው ውድድር ወደ ጥሎ ማለፍ ምዕራፍ ተሸጋግሯል። ከ24ቱ ሀገራት 16ቱ በሞሮኮ ሲቆዩ ስምንቱ ወደ ሀገራቸው ተመልሰዋል። በምድብ በተደረጉ 24 ጨዋታዎች 87 ግቦች መቆጠራቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል። በየጨዋታዎቹ በአማካይ ከሶስት ግቦች በላይ ተቆጥረዋል። ጨዋታዎቹ በጎል የተንበሸበሹ እና ማራኪ እንቅስቃሴ የተደረገባቸው ናቸው። የሞሮኮው አዩብ ኤል ካቢ ኮሞሮስ እና ዛምቢያ ላይ በመቀስ ምት ካስቆጠራቸው ድንቅ ግቦች አንስቶ የኮትዲቯሩ አማድ ዲያሉ ካሜሮን ላይ ከፍጹም ቅጣት ምት ክልል ውጪ ከመረብ ላይ እስካገናኛት ግሩም ጎል በርካታ ማራኪ ጎሎችን በምድብ ጨዋታዎች ለመመልከት ተችሏል። አይኖች ሁሉ ወደ ጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ባማተሩበት ወቅት ሌላኛው ትኩረት የሳበው ጉዳይ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት ጉዳይ ነው። የሞሮኮዎቹ አዩብ ኤል ካቢ እና ብራሂም ዲያዝ እንዲሁም የአልጄሪያው ሪያድ ማህሬዝ በተመሳሳይ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር የኮከብ ግብ አግቢነቱን በጋራ እየመሩ ይገኛሉ። 12 ተጫዋቾች በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን በማስቆጠር ይከተላሉ። ናይጄሪያውያኑ አዴሞላ ሉክማን እና ራፋኤል ኦንዬዲካ፣ የሴኔጋሎቹ ኒኮላስ ጃክሰን እና ቼሪፍ ንዳዬ፣ የግብጹ መሐመድ ሳላህ፣ ደቡብ አፍሪካውያኑ ላይል ፎስተር እና ኦስዊን ፍሊፕስ፣ የኮትዲቯሩ አማድ ዲያሎ፣ የአልጄሪያው ኢብራሂም ማዛ፣ የቱኒዚያው ኤሊያስ አቹሪ፣ የማሊው ላሲን ሲናዮኮ እና የሞዛምቢኩ ጌኒ ካታሞ በተመሳሳይ ሁለት ሁለት ግቦችን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። ሁለት ግቦችን ያስቆጠሩት የናይጄሪያው አዴሞላ ሉክማን እና የደቡብ አፍሪካው ላይል ፎስተር በተመሳሳይ ሁለት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችተው አቀብለዋል። የኮከብ ግብ አግቢ ማን ይሆናል? የሚለው ጉዳይ በቀጣይ የውድድሩ ጎዞ ምላሽ ያገኛል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል 
Jan 3, 2026 66
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 25/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከፋሲል ከነማ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዳማ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 12 ጨዋታዎች አምስቱ ሲያሸንፍ በሁለቱ ተሸንፏል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ቡድኑ በ20 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ በሊጉ ካደረጋቸው 12 ጨዋታዎች መካከል ስድስቱን ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ስድስት ጊዜ ተጋርቷል። በ24 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ እስከ አሁን ሽንፈት ያላስተናገደው ብቸኛ ክለብ ፋሲል ከነማ ነው። ፋሲል ከነማ ጨዋታውን ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ከሲዳማ ቡና ይረከባል። በሌላኛው መርሃ ግብር አርባምንጭ ከተማ ከሃዋሳ ከተማ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ እስከ አሁን 12 ጨዋታዎችን አከናውኖ ስድስት ጊዜ ሲሸነፍ በተመሳሳይ በስድስቱ አቻ ወጥቷል። በአምስት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ እስከ አሁን ምንም ድል ያላስመዘገበው ብቸኛው ክለብ አርባምንጭ ከተማ ነው። በውድድር ዓመቱ ካደረጋቸው 12 ጨዋታዎች መካከል ስድስቱን ያሸነፈው ሃዋሳ ከተማ በበኩሉ አራት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። ቡድኑ በ20 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ የመጀመሪያ ሶስት ነጥቡን ለማግኘት ሃዋሳ ከተማ ደግሞ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ20 ነጥብ አምስተኛ፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በዘጠኝ ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። ቅዱስ ጊዮርጊስ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 9 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጨዋታውን ያደርጋል። የ16 የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ18 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ወላይታ ድቻ በ11 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቅዱስ ጊዮርጊስ ከአራት ተከታታይ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ተገጣሚው ወላይታ ድቻ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም። የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ታህሳስ 27 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚቆይ የሊጉ አክሲዮን ማህበር መረጃ ያመለክታል። ሲዳማ ቡና ሊጉን በ25 ነጥብ እየመራ ነው።
የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል
Jan 3, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከሁለት ቀናት እረፍት በኋላ ዛሬ በጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች ይመለሳል። በታንጀር ስታዲየም ሴኔጋል ከሱዳን ምሽት አንድ ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። ሴኔጋል በምድብ አራት በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ በመሆን ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። በምድብ አምስት የነበረችው ሱዳን በሶስት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ በምርጥ ሶስተኝነት 16 ውስጥ ገብታለች። ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። በሌሎች ውድድሮች ላይ ሰባት ጊዜ ተገናኝተው ሴኔጋል አራት ጊዜ ስታሸንፍ ሶስት ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። ሴኔጋል በጨዋታዎቹ ላይ ስምንት ግቦችን ስታስቆጥር ሱዳን አንድ ጎል ብቻ ከመረብ ላይ አሳርፋለች። የአፍሪካ ዋንጫ መስራቿ ሱዳን ለመጀመሪያ ጊዜ ሴኔጋልን ለማሸነፍ ትጫወታለች። በሌላኛው የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ማሊ ከቱኒዚያ ምሽት አራት ሰዓት ላይ በመሐመድ አምስተኛ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።   ማሊ በምድብ አንድ በሶስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በምድቧ ያደረጋቻቸውን ሶስት ጨዋታዎች አቻ ወጥታለች። በምድብ ሶስት ተደልድላ ጨዋታዋን ያደረገችው ቱኒዚያ በአራት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅለች። ሁለቱ ቡድኖች ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ዋንጫ አራት ጊዜ ተገናኝተዋል። ማሊ ሁለት ጊዜ ስታሸንፍ በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ቱኒዚያ እ.አ.አ በ1994 ባዘጋጀችው 19ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው ማሊ ፈርናንድ ኩሊባሊ እና በሞቢዶ ሲዲቤ ግቦች 2 ለ 0 አሸንፋለች። ሀገራቱ ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት ኮትዲቯር ከሁለት ዓመት በፊት ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በምድብ አምስት ተገናኝተው አንድ አቻ ተለያይተዋል። ሃምዛ ራፊያ ለቱኒዚያ፣ ላሲን ሲናዮኮ ለማሊ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሲናዮኮ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ለማሊ ብሄራዊ ቡድን እየተጫወተ ይገኛል። የዛሬ ጨዋታዎች አሸናፊ ሀገራት በሩብ ፍጻሜው ይገናኛሉ። የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር እስከ ታህሳስ 28 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የሊጉ መሪ አርሰናል ከቦርንማውዝ ጋር ይጫወታል
Jan 3, 2026 85
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 25/2018 (ኢዜአ):- የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ20ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል። በዕለቱ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 2 ሰዓት ከ30 ላይ በቫይታሊቲ ስታዲየም ቦርንማውዝ ከአርሰናል ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ቦርንማውዝ በ23 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል።አርሰናል በ45 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ባለሜዳው ቦርንማውዝ ባለፉት 10 የሊግ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ተጋጣሚው አርሰናል ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች አሸንፏል። ጨዋታው ቦርንማውዝ ከሁለት ወር በላይ የዘለቀ ያለማሸነፍ ጉዞውን ለመቀልበስ፣ አርሰናል መሪነቱን ለማጠናከር የሚያደርጉት ነው ። አርሰናል ካሸነፈ ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሰባት ከፍ ያደርጋል። በሌሎች መርሃ ግብሮች በሊጉ ሶስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አስቶንቪላ ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር ጨዋታውን ያደርጋል። ብራይተን ከበርንሌይ እና ዎልቭስ ከዌስትሃም ዩናይትድ በተመሳሳይ ምሽት 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ።
ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ዋንጫ
Jan 2, 2026 232
ክፍል ሁለት የቀጠለ የኢትዮጵያ ዘጠነኛ ተሳትፎ በአህጉራዊው መድረክ እ.አ.አ 1982 ኢትዮጵያ በሊቢያ አስተናጋጅነት በተካሄደው 13ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለዘጠነኛ ጊዜ ተሳትፎዋን ማድረግ ቻለች። በውድድሩ ላይ አሁንም ስምንት አገራት ተሳትፈዋል።   ኢትዮጵያ በምድብ ሁለት ከአልጄሪያ፣ዛምቢያና ናይጄሪያ ጋር ተደልድላ ጨዋታዎቿን አድርጋለች። በምድብ ጨዋታዎቹ በናይጄሪያ 3 ለ 0 እንዲሁም በዛምቢያ 1 ለ 0 የተሸነፈች ሲሆን ከአልጄሪያ ጋር ያለ ምንም ግብ አቻ ተለያይታለች። ኢትዮጵያ በምድቧ አንድ ነጥብ ብቻ በመያዝ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ ይዛ አጠናቃለች። በፍጻሜው ጨዋታ ጋና ሊቢያን በመለያ ምት በማሸነፍ ለሶስተኛ ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫን አንስታለች። ኢትዮጵያ ከ31 ዓመት በኋላ ወደ አፍሪካው ዋንጫ የተመለሰችበት ታሪካዊ ሁነት ኢትዮጵያ ከ13ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በኋላ በአህጉራዊው የእግር ኳስ ውድድር መድረክ ለመሳተፍ ሶስት አስርት ዓመታታን መጠበቅ ግድ ሆኖባታል። በነዚህ 30 ዓመታት ጊዜ ውስጥ 15 የአፍሪካ ዋንጫ ውድድሮች ተካሄደዋል። እ.አ.አ በ2013 በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከ31 ዓመት በኋላ ወደ ውድድሩ ዳግም ተመለሰች። ኢትዮጵያ ወደ አፍሪካ ዋንጫው ያለፈችበት መንገድ ልብ አንጠልጣይ ነበር።   ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2012 በውድድሩ ላይ ለመሳተፍ ከሱዳን ጋር ባደረገችው የመጨረሻ ዙር የደርሶ መልስ ጨዋታ በመጀመሪያ ዙር ኦምዱርማን ላይ 5 ለ 3 በሆነ ውጤት ተሸንፋለች። ሱዳን ጨዋታውን ያሸነፈችው በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች በተቆጠሩ ሁለት አጨቃጫቂ የፍጹም ቅጣት ምት በግቦች ነበር። ጥቅምት 4 2004 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስታዲየም ለሚደረገው የመልስ ጨዋታ በስታዲየሙ ዙሪያ ከእኩለ ሌሊት ጀምሮ በርካታ ተመልካች ተሰልፎ ነበር። ጨዋታው በመጀመሪያው አጋማሽ ያለ ምንም መጠናቀቁ በስታዲየሙ የተገኘውን ተመልካች ጭንቅ ውስጥ ከቶ ነበር። ጭንቀቱ በስታዲየሙ ላሉት ብቻ ሳይሆን በቴሌቪዥን መስኮት ለሚከታተሉት በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንም ነበር። በሁለተኛው አጋማሽ የተሻለ እንቅስቃሴ ያደረጉት ዋልያዎቹ አዳነ ግርማ ባስቆጠራት ግብ መሪ መሆን ቻሉ። ይሁንና ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫው ለመሳተፍ አንድ ተጨማሪ ጎል ያስፈልጋታል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የቀድሞ አጥቂ ሳላዲን ሰዒድ ወሳኟን ሁለተኛ ግብ ከመረብ ላይ አሳረፈ። ግቡ ሲቆጠር በስታዲየሙ ተመልካቾች ላይ የነበረው ስሜት በከፍተኛ ደስታ የተሟላ ሲሆን ስሜታቸውንብ በእንባ የገለጹም ነበሩ። ጨዋታው በድምር ውጤት 5 ለ 5 ተጠናቆ ከሜዳ ውጪ ብዙ ባስቆጠረ በሚል ኢትዮጵያ ከ31 ዓመት በኋላ ዳግም ወደ አፍሪካ ዋንጫ መመለስ ቻለች። ከጨዋታው በኋላ በአዲስ አበባ ስታዲየም፣በመስቀል አደባባይና በመዲናዋ የተለያዩ አውራ ጎዳናዎች፣መንደሮችና የተለያዩ አካባቢዎች እንዲሁም በመላው ኢትዮጵያ ባሉ ክፍሎች የነበረው የደስታ ስሜትና ፈንጠዝያ የሚረሳ አልነበረም። በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያንም የደስታው ተቋዳሽ ነበሩ።   ኢትዮጵያን ከ31 ዓመት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫው እንድትመለስ ያደረጉት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ነበሩ። ደቡብ አፍሪካ ባዘጋጀችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ 16 አገራት በስድስት ምድብ ተከፍለው ጨዋታቸውን አድርገዋል። ኢትዮጵያም በምድብ ሶስት ከቡርኪናፋሶ፣ናይጄሪያና ዛምቢያ ጋር ተደልድላ ጨዋታዋን አድርጋለች። በመጀመሪያ ጨዋታዋ ኢትዮጵያ ከዛምቢያ ጋር አንድ አቻ ተለያይታለች። አዳነ ግርማ በ65ኛው ደቂቃ ለኢትዮጵያ ግቡን አስቆጥሯል። በሁለተኛው ጨዋታ ኢትዮጵያ በቡርኪናፋሶ የ4 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዳለች። በምድቡ የመጨረሻ ጨዋታ ኢትዮጵያ በናይጄሪያ 2 ለ 0 ተሸንፋለች። ውጤቶቹን ተከትሎ ኢትዮጵያ በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን አራተኛ ደረጃ ይዛ ከምድቧ ሳታልፍ ቀርታለች። ኢትዮጵያ ከ31 ዓመት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ብትመለስም በውድድሩ ላይ ያስመዘገበችው ውጤትና ያሳየችው ብቃት የእግር ኳስ ቤተሰቡን ያስደሰተ አልነበረም። ይሁንና ብሔራዊ ቡድኑ ከደቡብ አፍሪካ ሲመለስ በአዲስ አበባ ስታዲየም በበርካታ ደጋፊዎች አቀባበል ተደርጎለታል። በፍጻሜው ጨዋታ ናይጄሪያ ቡርኪናፋሶ 1 ለ 0 በማሸነፍ የአፍሪካን ዋንጫን ለሶስተኛ ጊዜ አንስታለች። ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ የተሳተፈችበት የአፍሪካ ዋንጫ   ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫ የተሳተፈችው እ.አ.አ በ2021 ካሜሮን ባዘጋጀችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነበር። ከስምንት ዓመታት በኋላ ወደ ውድድሩ የተመለሰችው ኢትዮጵያ በምድብ አንድ ከአዘጋጅ አገር ካሜሮን፣ቡርኪናፋሶና ኬፕቨርዴ ጋር ተደልድላ ጨዋታዋን አድርጋለች። ኢትዮጵያ በመጀመሪያ የምድብ ጨዋታዋ በኬፕቨርዴ 1 ለ 0 ተሸንፋለች። በሁለተኛው ጨዋታ ዋልያዎቹ በአዘጋጇ አገር ካሜሮን 4 ለ 1 ተሸንፈዋል። በጨዋታው ኢትዮጵያ አጥቂው ዳዋ ሁቴሳ በአራተኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ መሪ መሆን ብትችልም ቪንሰንት አቡበከርና ቶኮ ኢካምቢ በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን በማስቆጠር የማይበገሩትን አንበሶች አሸናፊ አድርገዋል። በወቅቱ በአሰልጣኝ ውበቱ የተመራው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በመጨረሻ የምድብ ጨዋታዋ ከቡርኪናፋሶ ጋር አንድ አቻ ተለያይታለች። ለብሔራዊ ቡድኑ ብቸኛዋን ግብ ያስቆጠረው ጌታነህ ከበደ በፍፁም ቅጣት ምት ነበር። ኢትዮጵያ በምድቡ አንድ ነጥብ ብቻ በማግኘት ከምድቧ የመጨረሻውን ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። የኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ በቁጥሮች ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ የ11 ጊዜ ተሳትፎ ኢትዮጵያ 31 ጨዋታዎችን አድርጋ 8ቱን ስታሸንፍ 19 ጊዜ ተሸንፋለች። አራት ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥታለች። በነዚህ 31 ጨዋታዎች ኢትዮጵያ 33 ግቦችን ስታስቆጥር 67 ጎሎችን አስተናግዳለች። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ በሰፊ ግብ ያሸንችባቸው ጨዋታዎች ሁለት ናቸው። እ.አ.አ በ1962 ራሷ አዘጋጅታ ራሷ በወሰደችው ሶስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ቱኒዚያና ግብጽን በተመሳሳይ 4 ለ 2 አሸንፋለች። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫው በሰፊ የግብ ልዩነት የተሸነፈችው እ.አ.አ በ1970 ሱዳን ባዘጋጀችው ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሲሆን በወቅቱ በኮትዲቭዋር 6 ለ 1 በሆነ ውጤት ተረታለች። ሰባተኛው የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ በውድድሩ ተሳትፎዋ ከፍተኛ ግብ ያስተናገደችበት ሲሆን 12 ጎሎች ተቆጥረውባታል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎዋ ከፍተኛ ግቦችን ያስቆጠረችባቸው ውድድሮች እ.አ.አ በ1952 እና በ1968 በቅደም ተከተል ሶስተኛውንና ስድስተኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ባዘጋጅበት ወቅት ነው። በነዚህ ውድድሮች ላይ በተመሳሳይ ስምንት ግቦችን አስቆጥራለች። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን ሶስት ጊዜ አዘጋጅታለች። ኢትዮጵያውያኖቹ አጥቂዎች ሉቺያኖ ቫሳሎና መንግስቱ ወርቁ በአፍሪካ ዋንጫ ላይ በተመሳሳይ 8 ግቦችን በማስቆጠር በአፍሪካ ዋንጫ የምንጊዜም የከፍተኛ ግብ አግቢዎች ዝርዝር ውስጥ 21ኛ እና 22ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። እንደ መውጫ   ኢትዮጵያ ሞሮኮ እየተካሄደ በሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አትሳተፍም። የአፍሪካ እግር ኳስ መስራችና ፈር ቀዳጅ እየተባለች የምትጠራው ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ተሳትፎዎቿ ከሰሜን፣ደቡብና ምዕራብ አፍሪካ አገራት ጋር ብርቱ ፉክክር በማድረግ መልካም የሚባል ውጤት አስመዝግባለች። ይሁንና ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በአፍሪካ ዋንጫ ያላት ተሳትፎ እየተቀዛቀዘ መጥቶ ብሔራዊ ቡድኑ ከምድቡ ማለፍ እየተሳነው ነው። የስፖርት ቤተሰቡና ተንታኞች ጠንካራ ብሔራዊ ቡድን መገንባት አለመቻሉ፣የእግር ኳስ እድገቱ ወደ ኋላ መቅረቱ፣ የአጥቂ መስመሩ ክፍል የአጨራረስ ድክመት፣ ለወጣት ተጫዋቾች እድል አለመስጠት፣የአሰልጣኞች በየጊዜው መለዋወጥ፣ለእገር ኳሱ የሚሰጠው ትኩረት የሚጠበቀውን ያህል አለመሆኑና እግር ኳሱ በስፖርቱ ባለፉ ሰዎች አለመመራቱን ጨምሮ በርካታ ምክንያቶች ይቀመጣሉ። ጠንካራና ተወዳዳሪ ቡድን የመገንባት ስራ ትኩረት ያሻዋል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2029 የሚካሄደውን 37ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ለማስተናገድ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጥያቄ ማቅረቧ የሚታወቅ ነው። በዚህም ውድድር ኢትዮጵያን ወክሎ የሚሳተፍ ጠንካራና አሸናፊ ብሔራዊ ቡድን መገንባት የሚያስችል "ሮድ 2029" የታዳጊዎች እግር ኳስ የስልጠና ፕሮጀክት ተጀምሯል፡፡ “ሮድ 2029"ን ለማሳካት ከኢትዮጵያ ከሁሉም አካባቢዎች 85 ብቃት ያላቸው ታዳጊዎች ተመርጠው ለዘጠኝ ወራት ስልጠና ወስደው ብቃት ያላቸው ተመርጠዋል፡፡ ከእነዚህ ታዳጊዎች መካከል 26ቱ በብቃታቸው ተመርጠው የ"ሮድ 2029" ግብን ማሳካት የሚያስችል የክፍል ውስጥ እና የሜዳ ላይ ስልጠና እየወሰዱ መሆኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።   ታዳጊዎቹ ኢትዮጵያ በህዳር ወር ባስተናገደችው ከ17 ዓመት በታች የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ የእግር ኳስ ማህበር ምክር ቤት ዞን (ሴካፋ) ተሳትፎ አድርጓል። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን በውድድሩ ላይ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ በሞሮኮ በሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ማለፉ ይታወቃል። "ሮድ 2029" የታዳጊዎች እግር ኳስ የስልጠና ፕሮጀክት በአሜሪካዊ እና ኢትዮጵያዊ አሰልጣኞች ጥምረት የሚካሄድ ሲሆን በኢትዮጵያ ዓለም የደረሰበትን ዘመናዊ ሥልጠና እየተሰጠ ይገኛል። በዲጂታል አማራጮች ተደግፎ በንድፈ ሀሳብና በተግባር የሚሰጥ ሥልጠና መሆኑን በማንሳት፤ በእስካሁኑ ሂደት ተስፋ ሰጭ ውጤት ታይቶበታል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የ2029 የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት እንድትመረጥ የቴክኒክ ጉዳዮችን ጨምሮ የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑንን ፌዴሬሽኑ አመልክቷል። ታዳጊዎችን እግር ኳስ ልማት፣ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን እንዲያሞሉ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች እና የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች መስፋት ተስፋ ሰጪ ጅማሮዎች ነው።   መንግስት የጀመራቸው ስራዎች በተጠናከረ መልኩ መቀጠል ይኖርባቸዋል። አጠቃላይ የእግር ኳሱ እደግት የስፖርት ባለድርሻ አካላትን የጋራ ትብብር ይጠይቃል። ተስፋ ሰጪ እና ብርሃን ፈንጣቂ ጅማሮዎችን ነገ ኢትዮጵያ በአፍሪካ እና በዓለም መድረክ በእግር ኳሱ ስኬታማ ለመሆን መሰረት የሚጥሉ ናቸው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም