ስፖርት
 በሻምፒዮናው ለሀገራችን የተሻለ ውጤት ለማምጣት ተዘጋጅተናል - አትሌቶች
Sep 27, 2023 96
አዲስ አበባ፤ መስከረም 16/2016(ኢዜአ)፦ በላቲቪያ ሪጋ በሚካሄደው የዓለም የጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና የተሻለ ውጤት ለማምጣት የሚያስችላቸውን ዝግጅት ማድረጋቸውን ኢዜአ ያነጋራቸው በሻምፒዮናው ላይ የሚሳተፉ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ገለጹ። በሻምፒዮናው ላይ የሚሳተፈው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ልዑካን ቡድን ትናንት ማምሻውን አሸኛኘት ተደርጎለታል። በሽኝት መርሐ-ግብሩ ላይ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር መስፍን ቸርነት፣ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ፣ የፌዴሬሽኑ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አመራሮችና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። አትሌቶች በውድድሩ የተሻለ ውጤት ለማግኘትና የኢትዮጵያን ሰንደቅ አላማ ከፍ አድርጎ ለማውለብለብ በጽናት መታገል እንዳለባቸው አምባሳደር መስፍን ገልጸዋል። በውድድሩ ለሚሳተፈው የአትሌቲክስ ቡድንም የመልካም ምኞት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ አትሌቶቹ የአየር ንብረቱንና ሌሎች ጫናዎችን ተቋቁመው በውድድሩ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል። ፌዴሬሽኑ ለአትሌቶቹ አስፈላጊውን ክትትልና ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። በሴቶች ግማሽ ማራቶን የምትሳተፈው አትሌት ፅጌ ገብረሰላማ፤ አትሌቶቹ ውድድሩ በሚካሄድበት ስፍራ ካለው ሞቃታማ የአየር ንብረት ጋር የሚጣጣም ልምምድ ሲያደርጉ መቆየታቸውን ገልጻለች። በውድድሩም የተሻለ ውጤት ለማምጣት መዘጋጀቷን ተናግራለች። በወንዶች ግማሽ ማራቶን የሚሳተፈው አትሌት ጀማል ይመር በበኩሉ፤ የአትሌቶች የመሰባሰቢያ ጊዜና ዝግጅት አጭር ቢሆንም የአየር ንብረቱን ተቋቁመው በቡድን ስራ ጥሩ ውጤት ለማምጣት መዘጋጀታቸውን ገልጿል። በግማሽ ማራቶን የሚሳተፈው የአትሌቲክስ ቡድን አሰልጣኝ ጌታመሳይ ሞላ፤ አትሌቶቹ ለሶስት ሳምንታት መዘጋጀታቸውንና ከሞቃታማ የአየር ንብረት ጋር በሚቀራረቡ ቦታዎች ልምምድ ሲያደርጉ መቆየታቸውን አብራርተዋል። የዝግጅት ጊዜው አጭር ቢሆንም በሻምፒዮናው የተሻለ ውጤት ለማምጣት መዘጋጀታቸውንም ነው አሰልጣኙ የገለጹት። የመጀመሪያው የዓለም የጎዳና ላይ ሩጫ ሻምፒዮና የፊታችን እሁድ መስከረም 20/2016 በላቲቪያ ሪጋ ይካሄዳል። በሻምፒዮናው ከ57 አገራት የተውጣጡ 347 አትሌቶች ይሳተፋሉ። 1 ማይል፣5 ኪሎ ሜትር እና የግማሽ ማራቶን በሁለቱም ጾታዎች ውድድር የሚካሄድባቸው ርቀቶች ናቸው። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው በ7 ሴቶች እና በ6 ወንዶች በድምሩ በ13 አትሌቶች ትወከላለች።  
ሉሲዎቹ ነጥብ ተጋርተዋል
Sep 22, 2023 158
አዲስ አበባ፤ መስከረም 11/2016 (ኢዜአ)፦ በሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ማጣሪያ ጨዋታውን ያደረገው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከብሩንዲ አንድ አቻ ተለያይቷል። በአዲስ አበባ አበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአጥቂ መስመር ተሰላፊዋ ረድኤት አስረሳኸኝ በ39ኛው ደቂቃ ያስቆጠረችው ግብ ቡድኑን መሪ አድርጋለች። ይሁንና ከእረፍት መልስ ካንያሙኔዛ ኤሪካ በ49ኛው ደቂቃ ከመረብ ያሳረፈችው ግብ ብሩንዲን አቻ አድርጓል። የሉሲዎቹ የፊት መስመር ተሳላፊ ሴናፍ ዋቁማ ከእረፍት በፊት በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብታለች። በሁለቱ አገራት የእግር ኳስ ፌዴሬሽኖች ስምምነት የቡድኖቹ የመልስ ጨዋታ መስከረም 15 ቀን 2016 ዓ.ም. በአበበ ቢቂላ ስታዲየም እንደሚከናወን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በአሰልጣኝ ፍሬው ኃይለገብርኤል የሚሰለጥነው ብሔራዊ ቡድኑ በደርሶ መልስ ጨዋታ ካሸነፈ በቀጣዩ ዙር ከዩጋንዳና አልጄሪያ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። በሞሮኮ አስተናጋጅነት የሚካሄደው 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ በሕዳር ወር 2024 ይካሄዳል።
የኢትዮጵያን እግር ኳስ ስፖርት ውጤት ማጣትን ለመፍታት ሳይንሳዊ የአሰለጣጠን ዘዴን መተግበር ይገባል- በኃይሉ በቀለ
Sep 22, 2023 142
አዲስ አበባ፤ መስከረም 11/2016 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን እግር ኳስ ስፖርት ውጤት ማጣት ችግር ለመፍታት ከታዳጊዎች ጀምሮ ሳይንሳዊ የአሰለጣጠን ዘዴን ተግባራዊ ማድረግ ይገባል ሲሉ የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ቴክኒካል አማካሪ በኃይሉ በቀለ ገለፁ። እግር ኳስ በኢትዮጵያ እጅግ ተወዳጅ ከሆኑና በበርካቶች ዘንድ በከፍተኛ ጉጉት ከሚዘወተሩ ስፖርቶች ቀዳሚው መሆኑ አያጠያይቅም፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካን እግር ኳስ በበላይነት የሚመራ ተቋም በአህጉሪቱ እንዲመሰረት ከፍተኛ አስተዋጽዖ አበርክታለች። እግር ኳስ በኢትዮጵያ አንድ ምዕተ-ዓመት የቆየና ሕዝባዊ መሠረት ያለው ስፖርት ቢሆንም በሚፈለገው መልኩ አላደገም። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የአዲስ አበባ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ቴክኒካል አማካሪ በኃይሉ በቀለ በኢትዮጵያ ያለው የእግር ኳስ አሰለጣጠን ዘይቤ ተመሳሳይ መሆኑን ይናገራሉ። ለዚህም ደግሞ ለታዳጊዎች፣ ለወጣቶችና ለጀማሪዎች በሚል እንደ ሀገር የተቀመጠ የሥልጠና መመሪያ አለመኖሩ ዋንኛ ምክንያት መሆኑን ገልፀዋል። የአሰለጣጠን ሥርዓቱ ዓለም የደረሰበትን ሳይንሳዊ አሠራር የተከተለ ባለመሆኑ ሳቢያም፤ በእግር ኳስ ስፖርት የሚፈለገውን ያህል ውጤት ማምጣት አልተቻለም ሲሉ አክለዋል። በፊፋ እንደተቀመጠውና በበርካታ የዓለም አገራት እንደሚሰራው የእግር ኳስ ሥልጠና ከስድስት ዓመት ጀምሮ ለህፃናት የሚሰጥ እንደሆነ አቶ በኃይሉ በቀለ አስረድተዋል። ሆኖም በኢትዮጵያ የታዳጊ ወጣቶች የእግር ኳስ ስፖርት ሥልጠና ከ13 እና ከ15 ዓመት የዕድሜ ክልል እንደሚጀምር ገልፀዋል። ይህም ታዳጊዎች በዕድሜያቸው ማግኘት የሚገባቸውን ሥልጠና እንዳያገኙና በአፍሪካ ውድድሮች ላይ ለሚመጡት ውጤቶች ደካማ መሆን መነሻ ምክንያት ናቸው ብለዋል። ይህንንም ለማስተካከል እያንዳንዱ የስፖርት ክለብ የራሱን መመሪያ ማዘጋጀት እንዳለበትና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በየደረጃው የአሰለጣጠን ሥርዓት መዘርጋት እንዳለበት አስረድተዋል። ሌሎች ሀገራትም የታዳጊ ወጣቶች የእግር ኳስ ስፖርት ሥልጠና መተግበሪያ እንዳላቸውና ኢትዮጵያም ሊኖራት እንደሚገባ ገልፀዋል። የታዳጊ ወጣቶች የእግር ኳስ ስፖርት ሥልጠና በኢትዮጵያ ከ1990 ዓ.ም ጀምሮ እየተካሄደ ይገኛል። ትንሹ የሥልጠና ዕድሜ ከ13 ዓመት በታች መሆኑ ግን ከታችኛው የዕድሜ ክልል ጀምሮ እንደማይሰራ ያሳያል። ስለዚህ የሚመለከታቸው የፌደራል ባህልና ስፖርት ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለዚህ ችግር መፍትሔ ሊያበጁለት ይገባል ብለዋል።    
ሉሲዎቹ የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታቸውን ዛሬ ያደርጋሉ
Sep 22, 2023 114
አዲስ አበባ፤ መስከረም 11/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ብሔራዊ ቡድን የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ማጣሪያ ጨዋታውን ዛሬ ከብሩንዲ አቻው ጋር በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ያካሂዳል ። እ.አ.አ 2024 በሞሮኮ አስተናጋጅነት የሚካሄደው 15ኛው የሴቶች ብሔራዊ ቡድን የማጣሪያ ጨዋታውን ዛሬ ከቀኑ 9 ሰዓት ያካሂዳል። በአሰልጣኝ ፍሬው ኃይለገብርኤል የሚሰለጥነው ብሔራዊ ቡድኑ፤ 26 ተጨዋቾችን በመያዝ ዝግጅቱን ከጳጉሜን 3 ቀን 2015 ዓ.ም. አንስቶ በኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ሲያደርግ ቆይቷል። ከአገር ውስጥ ቡድኖች ጋርም የተለያዩ የአቋም መፈተሻ ጨዋታዎችን አድርጓል። ለዛሬው ጨዋታ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም አከናውኗል። በ38 ዓመቱ ብሩንዲያዊ ጉስታቭ ኒዮንኩሩ የሚሰለጥነው የብሩንዲ ብሔራዊ ቡድን ላለፉት ጥቂት ሳምንታት ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቷል። በዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማኅበር(ፊፋ) ወርሃዊ በሴቶች የአገራት የእግር ኳስ ደረጃ ኢትዮጵያ 124ኛ እንዲሁም ብሩንዲ 175ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ሴንያሴንግ ሴፌ ከቦትስዋና የሁለቱን ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመራሉ። በሁለቱ አገራት የእግር ኳስ ፌዴሬሽኖች ስምምነት የቡድኖቹ የመልስ ጨዋታ መስከረም 15 ቀን 2016 ዓ.ም. በአበበ ቢቂላ ስታዲየም እንደሚከናወን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የመልሱ ጨዋታ በአዲስ አበባ የሚከናወነው ብሩንዲ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) መስፈርቶች የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ማስተናገድ የሚችል ስታዲየም የሌለው እንደሆነ ገልጿል። በአንጻሩ የአበበ ቢቂላ ስታዲየም የካፍን መስፈርቶች ያሟላ መሆኑን ፌዴሬሽኑ አመልክቷል። ሉሲዎቹ በደርሶ መልስ ጨዋታ ካሸነፉ በቀጣዩ ዙር ከዩጋንዳና አልጄሪያ አሸናፊ ጋር ይጫወታሉ። ሞሮኮ እ.አ.አ በ2024 በምታስተናግደው 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለመሳተፍ 40 አገራት የማጣሪያ ጨዋታቸውን በማድረግ ላይ ይገኛሉ። የማጣሪያ ጨዋታዎቹ በሁለት ዙር የደርሶ መልስ ጨዋታዎች የሚከናወን ሲሆን ከአስተናጋጇ አገር ሞሮኮ ውጭ 11 አገራት የተሳትፎ ቦታውን ለማግኘት ይፋለማሉ። በአፍሪካ ዋንጫ ውድድሩ ላይ 12 አገራት እንደሚሳተፉ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን(ካፍ) አስታውቋል።  
የአፍሪካ ስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽኖች የመሪዎችና የአመራር አካዳሚ ጉባኤ በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Sep 15, 2023 347
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 4/2016 (ኢዜአ) ፦ የአፍሪካ ስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽኖች የመሪዎችና የአመራር አካዳሚ ጉባኤ በሚቀጥለው ሣምንት በአዲስ አበባ ሊካሄድ ነው። ጉባኤው ከመስከረም 07/2016 ዓ.ም ጀምሮ ሦስት ተከታታይ ቀናት የሚሄድ ሲሆን ከ39 የአፍሪካ አገራት የተውጣጡ የዘርፉ ተዋናዮችና ሌሎች እንግዶች በጉባኤው ይሳተፋሉ ተብሏል። የአፍሪካ ስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽን ይህንን ጉባኤው የተሳካ ለማድረግና በቀጣይ በሌሎች ጉዳዮች በትብብር ለመሥራት ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር ዛሬ ሥምምነት ፈጽሟል። ሥምምነቱን በኢትዮጵያ አየር መንገድ የተቀናጀ የማርኬቲንግ ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ንጉሱ ወርቁና የአፍሪካ ስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ቻርለስ ንያምቤ ፈርመውታል። የኢትዮጵያ ስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ምህረት ንጉሴ የአፍሪካ ስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽኖች የአመራርና የአካዳሚ ጉባኤን ለማስተናገድ ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል።   በጉባኤውም በዓለም አቀፍ የስፔሻል ኦሊምፒክ ሕግጋት፣ አሰራሮችና በተካሄዱ ውድድሮች ላይ የነበሩ ጥንካሬን ድክመቶች ላይ በመምከር የቀጣይ ማሻሻያ ርምጃ እንደሚቀመጥ አንስተዋል። የኢትዮጵያ ስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽን ሥራ አስፈፃሚ ፈሪድ መሃመድ፤ በጉባኤው የተገኙ አዳዲስ ልምዶች ላይ ምክክር በማድረግ የአዕምሮ ውስንነት ተጠቂ የሆኑ ዜጎችን ስፖርታዊ ተሳትፎ ማሳደግ የጉባኤው ዓላማ መሆኑን ገልጸዋል።   በኢትዮጵያ አየር መንገድ የተቀናጀ የማርኬቲንግ ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ንጉሱ ወርቁ፤ ሥምምነቱ በአዲስ አበባ በሚካሄደው የአፍሪካ ስፔሻል ኦሊምፒክ ጉባኤ የሚታደሙ ተሳታፊዎችን ማጓጓዝ፣ የስካይ ላይት ሆቴል መስተንግዶና ሌሎች ቀጣይ ትብብሮችን ያካትታል ነው ያሉት።   የአፍሪካ ስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ቻርለስ ንያምቤ፤ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር የተደረሰው ሥምምነት ጉባኤውን በስኬት ለማስተናገድ ጠቀሜታ አለው ብለዋል።   የስፔሻል ኦሊምፒክ ፌዴሬሽን እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1968 የተመሰረተው ሲሆን የአዕምሮ ውስንነት ያለባቸውን ዜጎች በስፖርታዊ ውድድሮች የሚያበረታታ ስፖርታዊ የውድድር አይነት ነው።  
የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ 307 ታዳጊዎችን ተቀብሎ ለማሰልጠን መዘጋጀቱን አስታወቀ
Sep 14, 2023 262
አዲስ አበባ፤ መስከረም 3/2016(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ በዘንድሮው ዓመት 307 ታዳጊዎችን ተቀብሎ በተለያዩ የስፖርት አይነቶች ለማሰልጠን መዘጋጀቱን የአካዳሚው ዋና ዳይሬክተር አንበሳው እንየው ገለጹ። በየዘርፉ ተመልምለው ለስልጠና የሚገቡ ስፖርተኞች ለአራት ዓመታት ስልጠና የሚሰጣቸው መሆኑ ታውቋል። የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ሀገርን በዓለም አቀፍ የስፖርት መድረኮች የሚወክሉ ብቃት ያላቸው ስፖርተኞችን በሳይንሳዊ ስልጠና በመታገዝ የማፍራት ተልዕኮ ይዞ እየሰራ ይገኛል።   በ24 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈው አካዳሚው በውስጡ ስታዲየም፣ ጅምናዚየም፣ የመማሪያና የመኝታ ክፍሎች እንዲሁም ዓለም አቀፍ ደረጃን ያሟላ የመዋኛ ገንዳ ያለው ነው። ከአስር ዓመት በፊት በ290 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው አካዳሚው በየዓመቱ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች ታዳጊ ስፖርተኞችን በመመልመል ስልጠና እየሰጠ ይገኛል። በአካዳሚው ሰልጥነው ስኬታማ ከሆኑ ስፖርተኞች መካከልም አትሌት ለሜቻ ግርማ (አትሌቲክስ)፣ ሰለሞን ቱፋ (በወርልድ ቴኳንዶ) እና ናርዶስ ሲሳይ (በማርሻል አርት) ይጠቀሳሉ። በ2016 ዓ.ም አካዳሚው በዘጠኝ የስፖርት አይነቶች 307 ስፖርተኞችን በመመልመል ለማሰልጠን ዝግጅት ማድረጉን የአካዳሚው ዋና ዳይሬክተር አንበሳው እንየው ገልጸዋል። ከሚሰለጥኑባቸው የስፖርት አይነቶች መካከልም አትሌቲክስ፣ እግር ኳስ፣ ወርልድ ቴኳንዶ፣ ብስክሌት፣ ቅርጫት ኳስ እና ሌሎችንም ጠቅሰዋል።   በመሆኑም እድሜያቸው ከ16 ዓመት በታች የሆኑ 3 ሺህ ታዳጊዎች መመዝገባቸውን አስታውሰው በተቀመጠው መስፈርት መሰረት 307ቱ ተለይተው ወደ አካዳሚው ለስልጠና ይገባሉ ብለዋል። ለስልጠና የሚገቡ ታዳጊዎች የሚለዩትም በእድሜ፣ በአካል ብቃት፣ በጤንነት ሁኔታ እና በስነ ልቦና ዝግጁነት መሆኑን ዘርዝረዋል። በዚህ መሰረትም የመጨረሻ የማጣሪያ ምልምላ ያለፉት ታዳጊዎች ለቀጣይ አራት ዓመታት በአዲስ አበባ እና በአሰላ ስፖርት አካዳሚ ይሰለጥናሉ ብለዋል። የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ከ2006 ዓ.ም ጀምሮ ካሰለጠናቸው ታዳጊዎች መካከል ከ250 በላይ ስፖርተኞችን በተለያዩ የስፖርት አይነቶች ለብሄራዊ ቡድን ማስመረጡን መረጃዎች ይጠቁማሉ።  
አብሮነት በሁሉም የስራ መስክ የድል መሰረት ነው - በ19ኛው የቡዳፔስት አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተሳታፊ አትሌቶች
Sep 11, 2023 223
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 6/2015 (ኢዜአ) ፦ አብሮነት በሁሉም የስራ መስክ የድል መሰረት ነው ሲሉ በ19ኛው የቡዳፔስት አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተሳታፊ አትሌቶች ተናገሩ። ዛሬ ጳጉሜን 6 የአብሮነት ቀን "በሕብር የተሰራች ሀገር" በሚል መሪ ሀሳብ እየተከበረ ይገኛል። ኢትዮጵያውያን በአብሮነት እሴት ድልና ተግዳሮቶችን በጋራ በማለፍ የሀገር ሕልውናን ማስጠበቅ ችለዋል። በየትውልዱ የነበሩ የአብሮነት እሴቶች ለሀገር ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ እና ስነ-ልቦናዊ ከፍታ መሰረት ሆነው፣ ኢትዮጵያውያን በየዘመኑ በድል ታጅበው እንዲዘልቁ አስችሏል። ከሀገር ክብርና ገጽታ አኳያ የአብሮነት ትሩፋት መካከል አንዱ የአትሌቲክስ ዘርፍ ሲሆን ላለፉት በርካታ አስርት ዓመታት በዓለም መድረክ ላይ የታየው ድል በዚህ በኩል ተጠቃሽ ነው፡፡ የሀገርን ሰንደቅ ዓላማ ይዘው የሚወዳደሩ አትሌቶች 'አረንጓዴው ጎርፍ' የተሰኘ ስያሜ እስኪሰጣችው ድረስ ለሀገራቸው ክብር ተባብረዋል፣ በተሰለፉበት ውድድርም አኩሪ ድል አስመዝግበዋል። በቅርቡ በሀንጋሪ ርዕሰ መዲና ቡዳፔስት በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተሳታፊዎችም በቡድን በመስራት የሀገር ስምና ክብር ከፍ እንዲል ብርቱ ትግል አድርገዋል፡፡ የሶስት ሺህ ሜትር መሰናክል ውድድር የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት እና በ19ኛው ቡዳፔስት ሻምፒዮና ላይ በሶስት ሺህ መሰናክል የብር ሜዳሊያ ያስገኘው አትሌት ለሜቻ ግርማ፣ ለሀገር መስዋዕትነት መክፈል ኩራት እንደሆነ ይገልጻል። በቡዳፔስት የዓለም ሻምፒዮና በሴቶች ማራቶን ውድድር በቡድን ስራ ትልቅ ሚና የነበራት አትሌት ፀሐይ ገመቹ በበኩሏ፣ ለሀገርና ህዝብ በማሰብ እስከመስዋዕትነት እንደምትሮጥ ትገልጻለች። በሻምፒዮናው በወንዶች ማራቶን የነሐስ ሜዳሊያ ያስገኘው አትሌት ልዑል ገብረስላሴም፣ የሀገር ድል በመናፈቅ በማንኛውም ውድድር ላይ ዋጋ መክፈል እንደሚያስፈልግ ይናገራል። በሴቶች ማራቶን ውድድር በኦሬጎኑ 18ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮን የወርቅ እንዲሁም በ19ኛው የቡዳፔስት የዓለም ሻምፒዮና ለኢትዮጵያ የብር ሜዳሊያ ያስገኘችው አትሌት ጎይቲቶም ገብረሥላሴም ይህን ሃሳብ ትጋራለች።   በውድድሩ ኢትዮጵያውያን በአብሮነት በመስራት ከወርቅ እስከ ነሐስ ሜዳሊያዎችን በመሰብሰብ ራስን እስከመሳት የሚያስችል ብርቱ ትንቅንቅ ማድረጋቸውንም አስታውሰዋል። በቡዳፔስቱ ውድድር በአየር ጸባዩ ሁኔታ ክብደት የተጠበቀው ውጤት ባይመጣም በአብሮነት እሴት አኩሪ ገድልና ድል ለማስመዝገብ በቡድን እንደሰሩ ተናግረዋል። በውድድሩ ሁሉንም ሜዳሊያዎች ለማምጣት የተደረገው ጥረት ባይሳካም በቀጣይ የአብሮነት ስራቸውን በማጠናከር ለሀገር አኩሪ ድል ለማስመዝገብ እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።
በአዲስ አበባ ከተማ ከመደመር ትውልድ መጽሃፍ ሽያጭ በተገኘ ገቢ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ እና የህጻናት መጫወቻ ስፍራዎች ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ
Sep 10, 2023 210
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2015(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ከመደመር ትውልድ መጽሃፍ ሽያጭ በተገኘ ገቢ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ እና የህጻናት መጫወቻ ስፍራዎች ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ፡፡ በመላ ሀገሪቱ "ኢትዮጵያ የትውልዶች ድምር" በሚል መሪ ሃሳብ ጳጉሜን 5 ቀን 2015 ዓ.ም የትውልድ ቀን እየተከበረ ይገኛል፡፡   በዛሬው እለትም የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከመደመር ትውልድ መጽሃፍ ሽያጭ በተገኘ ገቢ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ እና የህጻናት መጫወቻ ስፍራዎች መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል፡፡ ከንቲባዋ በዚሁ ጊዜ፤ የከተማ አስተዳደሩ ለወጣቶች የስፖርት ማዘውተሪያ ቦታዎችን በስፋት በመገንባት ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ሰባት የህጻናት መጫወቻና የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን የጠቀሱት ከንቲባዋ በዛሬው ዕለት ደግሞ አምስት ማዘውተሪያዎች መመረቃቸው ተናግረዋል፡፡   ለአገልግሎት ክፍት የሆኑ ስፍራዎቹ ሀገርን የሚያስጠሩ ስፖርተኞችን ለማፍራት እንደሚያስችል ገልጸው ሃብቶችን በአግባቡ እንዲጠብቋቸውና እንዲጠቀሙባቸው መልዕክታቸውን አስተላለፈዋል። የኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ዋና ስራ አስፈፃሚ ንጋቱ ዳኛቸው፤ ከመደመር ትውልድ መጽሃፍ ሽያጭ በተገኘ 30 ሚሊየን ብር የህጻናት መጫወቻና ደረጃውን የጠበቀ ማዝወተሪያ መገንባት መቻሉን ገልጸዋል። ኢንተርናሽናል የቴኳንዶ አሰልጣኝ ሳቦን ቢላል አሕመድ፤ በበኩሉ የከተማ አስተዳደሩ ለስፖርት ማዘወተሪያ ስፍራዎች የተሰጠው ትኩረት አስደሳች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይህም የከተማዋ ነዋሪዎች የአካል ብቃት እንቅስቃሴ እንዲያዘወትሩ ምቹ እድል መፍጠሩን ጠቅሰው፤ ትውልዱን በስፖርትና ስነምግባር ለማነጽ የተጀመረው ስራ በአዲሱ ዓመትም ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቋል። በምረቃ ስነ ስርዓቱ ላይ ከንቲባዋ ለወጣቶች የስፖርት ቁሳቁስና ልዩ ልዩ ሽልማቶችን አበርክተዋል።  
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ዛሬ ከግብጽ ጋር ትጫወታለች
Sep 8, 2023 296
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2015(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በኮትዲቭዋር አስተናጋጅነት ለሚካሄደው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ የመጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታውን ዛሬ ከግብጽ ጋር ያደርጋል። የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታ በካይሮ 'June 30 Stadium' ከምሽቱ 1 ሰዓት ላይ ይከናወናል። በጊዜያዊ ዋና አሰልጣኝ ኢንስትራክተር ዳንኤል ገብረማርያም የሚመራው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለጨዋታው ከነሐሴ 23 እስከ 28/2015 በአዲስ አበባ ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቷል። ቡድኑ ለዛሬው ጨዋታ የመጨረሻ ልምምዱን ጨዋታውን በሚያደርግበት 'June 30 Stadium' አከናውኗል። ሁሉም የስብስቡ አባላትም በተሟላ ጤንነት ልምምዳቸውን እንዳደረጉ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።   ኢንስትራክተር ዳንኤል ገብረማርያም ከጨዋታው በፊት በሰጡት መግለጫ ኢትዮጵያ በማጣሪያው ከምድቧ ብትወድቅም ቡድናቸው ጨዋታውን ለቀጣይ የዓለም ዋንጫና የአፍሪካ አገራት እግር ኳስ ሻምፒዮና (ቻን) የማጣሪያ ውድድሮች መዘጋጃ እንደሚጠቀምበት ገልጸዋል። በመጀመሪያ የማጣሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ግብጽን 2 ለ 0 ማሸነፏን አውስተው፤ በዛሬው ጨዋታም መልካም ውጤት ለማምጣት ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል። በ53 ዓመቱ ፓርቹጋላዊ አሰልጣኝ ሩዊ ቪቶሪያ የሚመራው የግብጽ ብሔራዊ ቡድን በማጣሪያው በምድብ አራት 12 ነጥብ በመያዝ ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፉ ይታወቃል። የ30 ዓመቱ ጋቦናዊ ፓትሪስ ታንጉይ ሜቢያሜ የሁለቱን ብሔራዊ ቡድኖች በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ በምድብ አራት የሚገኘው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በአራት ነጥብ የመጨረሻውን ደረጃ የያዘ ሲሆን ከምድቡ አስቀድሞ መውደቁ የሚታወስ ነው። በዚሁ ምድብ ጊኒ ግብጽን ተከትላ ለአፍሪካ ዋንጫ ማለፏ ይታወቃል።   ሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች በሐምሌ ወር 2014 በማላዊ ቢንጉ ብሔራዊ ስታዲየም ባደረጉት የማጣሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ በሽመልስ በቀለና ዳዋ ሆቴሳ ግቦች ግብጽን 2 ለ 0 ማሸነፏ የሚታወስ ነው።    
ኢትዮጵያ በሩጫ ውድድር ያላትን አስደናቂ  የድል ታሪክ በሌሎች የአትሌቲክስ ዘርፎች ለመድገም በትኩረት ሊሰራ ይገባል - የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ቀጄላ መርዳሳ
Sep 4, 2023 327
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 29/2015 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በሩጫ ውድድር የተመዘገቡ አስደናቂ ድሎችን በሌሎች የአትሌቲክስ ዘርፎች ለመድገም በትኩረት መስራት እንዳለበት የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ቀጄላ መርዳሳ ገለጹ። በሀንጋሪ ቡዳፔስት በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ለተሳተፉ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ትናንት የዕውቅና እና ሽልማት መርሀ ግብር ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የባህልና ስፖርት ሚኒስትር አቶ ቀጄላ መርዳሳ፣ በተሰማሩበት ሙያ ታላቅ ገድል እና የላቀ ውጤት ያስመዘገቡ ሰዎችን መሸለምና ዕውቅና መስጠት አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በአትሌቲከስ ሻምፒዮናው ኢትዮጵያን ከፍ ላደረጉ አትሌቶች የተሰጠው ሽልማት ዓላማውም በቀጣይ የተሻለ ውጤት እንዲያመጡና ለትውልድ አርዓያ እንዲሆኑ ነው ብለዋል። በቡዳቤስት ለተገኘው ውጤት በውድድሩ የነበረው የቡድን ስራ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ በቀጣይ ያሉ ክፍቶችን በማረም ለተሻለ ውጤት መሰራት እንደሚገባ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአትሌቲክስ ዘርፍ የረዥም ዘመን የድል አድራጊነት ዕውቅና ያላት ሀገር መሆኗን ገልጸው በሌሎች የውድድር መስኮችም ይህንን መድገም እንደሚያስፈልግ አንስተዋል። ለዚህም የኢትዮጵያ አትሌቲከስ ፌደሬሽን በቀጣይ ከሩጫ ውድድር ባሻገር በሌሎች የአትሌቲክስ ስፖርታዊ ውድድሮች ላይ በትኩረት መስራት አለበት ነው ያሉት። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ በበኩሏ፤ በቡዳፔስት በአስቸጋሪ አየር ሁኔታ ውስጥ የተገኘው ውጤት እንደተጠበቀው ባይሆንም ትልቅ ውጤት ነበር ብላለች። በውድድሩ የታዩ ደካማ ጎኖችን በማረም በቀጣይ በፓሪስ በሚካሄደው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች ውድድር ላይ የተሻለ ውጤት ለማምጣት እንደሚሰራ አረጋግጣለች።    
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች እግር ኳስ ክለብ ለካፍ የሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ  ማለፍ አልቻለም
Aug 30, 2023 378
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 24/2015 (ኢዜአ) ፦ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች እግር ኳስ ክለብ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን ማጣሪያ ዛሬ ባደረገው የፍጻሜ ጨዋታ በታንዛንያው ጄኪቴ ኩዊንስ በመለያ ምት ተሸንፏል። በዩጋንዳ አስተናጋጅነት ከነሐሴ 6/2015 ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው የካፍ የሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የሴካፋ ዞን የማጣሪያ ውድድር ዛሬ ፍጻሜውን አግኝቷል። በ ‘FUFA Technical Center Stadium’ በተካሄደው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክና የታንዛንያው ጄኪቴ ኩዊንስ ጨዋታ በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜና በጭማሬ 30 ደቂቃ ግብ አልተቆጠረም። አሸናፊውን ለመለየት ጨዋታው ወደ መለያ ምት ያመራ ሲሆን ጄኪቴ ኩዊንስ 5 ለ 4 በማሸነፍ የሴካፋ ዞንን ወክሎ በኮትዲቭዋር አቢጃን በሕዳር ወር 2016 በሚካሄደው ሶስተኛው የካፍ የሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ መሳተፉን አረጋግጧል። በአሰልጣኝ ብርሃኑ ግዛው የሚመራው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለተኛ ደረጃን ይዞ ውድድሩን አጠናቋል። በዩጋንዳ ካምፓላ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በስታዲየሙ በመገኘት ለቡድኑ ድጋፋቸውን ሰጥተዋል። ከፍጻሜ ጨዋታ በፊት በተደረገው የደረጃ ጨዋታ የብሩንዲው ቡጃ ኩዊንስ የኬንያውን ቪሂጋ ኩዊንስን 1 ለ 0 በማሸነፍ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሴቶች እግር ኳስ ቡድን ከዚህ ቀደም በኬንያና ታንዛንያ በተካሄዱ የካፍ የሴቶች ሻምፒዮንስ ሊግ የማጣሪያ ውድድሮች በቅደም ተከተል ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው።
በፈረንሳይ ፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የተሻለ ውጤት ለማምጣት በትኩረት ይሰራል - ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ
Aug 29, 2023 292
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 23/2015 (ኢዜአ) ፡- በቀጣዩ ዓመት በፈረንሳይ ፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የተሻለ ውጤት ለማምጣት በትኩረት እንደሚሰራ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ ገለጸች። በሃንጋሪ፤ ቡዳፔስት በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ለተሳተፈው የአትሌቲክስ ቡድን አቀባበል ተደርጎለታል። ልዑኩ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርስ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ቀጄላ መርዳሳ፣የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ኤርጎጌ ተስፋዬ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች አቀባበል አድርገውለታል። አትሌቶች በአዲስ አበባ ዋና ዋና ጎዳናዎች ላይ በመዘዋወር ከሕዝቡ ጋር ደስታቸውን ተጋርተዋል። በሃንጋሪ ቡዳፔስት በተካሄደው ሻምፒዮና ላይ ኢትዮጵያ በ2 ወርቅ፣ 4 ብርና 3 ነሃስ በድምሩ ዘጠኝ ሜዳሊያዎችን መሰብሰብ ችላለች። ኢትዮጵያ በደረጃ ሰንጠርዥም ከአፍሪካ 2ኛ ከዓለም 6 ደረጃን በመያዝ ማጠናቀቅ ችላለች። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ በዚሁ ጊዜ እንደገለጸችው፤ በውድድሩ ኢትዮጵያዊያን በአንድነትና በመተባበር ጥሩ ውጤት አምጥተዋል።   በጥረታችሁ የኢትዮጵያን ስም ከፍ ያደረጋችሁ አትሌቶች፣ አሰልጣኞች የአትሌቲክሱ ማኅበረሰብ ምስጋና ይገባቹሃል፤ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽንም ምስጋና ያቀርባል ብላለች። እ.አ.አ በ2024 በፈረንሳይ ፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የተሻለ ውጤት ለማምጣት በልዩ ሁኔታ እንደሚሰራም ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ተናግራለች። የአትሌቲክስ ልዑክ ቡድኑ መሪ አትሌት ገዛኸኝ አበራ በበኩሉ በውድድሩ ውጤታማ ለመሆን ከ800 ሜትር እስከ ማራቶን ድረስ ዝግጅት በማድረግ መሳተፍ መቻሉን ገልጿል። "በውድድሩ ቆይታ ዘጠኝ ሜዳሊያ ይዘን መጥተናል፤ ውጤቱ የመጣው ከ 35 እስከ 37 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ ሙቀት ባለው የአየር ጸባይ ነው" ያለው ቡድን መሪው ውጤቱ የኢትዮጵያዊያን አትሌቶች ተጋድሎ የታየበት ነው ብሏል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ቀጄላ መርዳሳ በበኩላቸው በውድድሩ አትሌቶቹ ያደረጉት ተጋድሎ የሚደነቅ ነው።   "የኢትዮጵያ ስም በእናንተ ተጠርቷል፤ በዓለም ዙሪያ ያሉ ሕዝቦች ትኩረታቸውን ኢትዮጵያ ላይ እንዲሆን በማድረጋችሁ ኮርተንባችኋል" ሲሉም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ፕሬዝዳንት ዶክተር አሸብር ወልደጊዮርጊስ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት በየዘርፉ ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት በትኩረት ሊሰራ ይገባል።   የአትሌቲክስ ማሰልጠኛዎችን ማጠናከር፣ መሮጫ መንገድ /ትራክ/ ያላቸውን ስታዲየሞችን መገንባትና የተደራጀ አትሌቲክስ ካምፕ ማዘጋጀት በአትሌቲክሱ ዘርፍ ውጤታማ ለመሆን በስፋት ሊሰራባቸው እንደሚገባም ነው አጽንኦት የሰጡት። አትሌት ልዑል ገብረ ሥላሴ በሃንጋሪ ቡዳፔስት በተካሄደው የዓለም የአትሌቲክስ ሻምፒዮና በማራቶን ሩጫ ውድድር ለኢትዮጵያ የነሃስ ሜዳሊያ አስገኝቷል። በቀጣይም ጠንክሮ በመስራት የኢትዮጵያን ሕዝብ ለመካስ ጥረት እንደሚያደርግም ነው ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት በሰጠው አስተያየት የገለጸው።                      
በቀጣዩ ዓመት በፈረንሳይ ፓሪስ ለሚካሄደው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች  የተሻለ ውጤት ለማምጣት ይሰራል -ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ
Aug 29, 2023 336
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 23/2015(ኢዜአ)፦ በቀጣዩ ዓመት በፈረንሳይ ፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የተሻለ ውጤት ለማምጣት በትኩረት እንደሚሰራ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ ቱሉ ገለጸች። በሃንጋሪ ቡዳፔስት በተካሄደው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ለተሳተፈው የአትሌቲክስ ቡድን አቀባበል ተደርጎለታል። ረዳት ኮሚሽነር ደራርቱ በዚሁ ወቅት እንዳለችው በውድድሩ ኢትዮጵያዊያን በአንድነትና በመተባበር ጥሩ ውጤት አምጥተዋል። በጥረታችሁ የኢትዮጵያን ስም ከፍ ያደረጋችሁ አትሌቶች ምስጋና ይገባቹሃል፤ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽንም ምስጋና ያቀርባል ብላለች። እ.አ.አ በ2024 በፈረንሳይ ፓሪስ በሚካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች የተሻለ ውጤት ለማምጣት በልዩ ሁኔታ እንደሚሰራም ነው የተናገረችው። የልዑካን ቡድኑ መሪ አትሌት ገዛኸኝ አበራ በውድድሩ ውጤታማ ለመሆን ከ800 ሜትር እስከ ማራቶን ድረስ ዝግጅት በማድረግ ለመሳተፍ መቻሉን ገልጿል። 'በውድድሩ ቆይታ ዘጠኝ ሜዳሊያ ይዘን መጥተናል ፤ውጤቱ የመጣው ከ35 እስከ 37 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ ሙቀት ላይ ተወዳድረን ነው' ሲልም ተናግሯል። የኢትዮጵያ ኦሊምፒክ ኮሚቴ ፕሬዝዳንት ዶክተር አሸብር ወልደጊዮርጊስ በበኩላቸው በአሁኑ ወቅት በየዘርፉ ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት እየተሰራ ነው። ከዚህ ውስጥም ማሰልጠኛዎችን ማጠናከርና የተደራጀ አትሌቲክስ ካምፕ ማዘጋጀት ዋነኞቹ እንደሆኑም ጠቅሰዋል። የባህልና ስፖርት ሚኒስትር አቶ ቀጄላ መርዳሳ እንዳሉት በውድድሩ አትሌቶቹ ያደረጉት ተጋድሎ የሚደነቅ ነው። 'የኢትዮጵያ ስም በእናንተ ተጠርቷል በዓለም ዙሪያ ያሉ ሕዝቦች ትኩረታቸውን ኢትዮጵያ ላይ እንዲሆን በማድረጋችሁ ኮርተንባችኋል' ብለዋል። 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች እ.አ.አ ከሐምሌ 26 እስከ ነሐሴ 11 /2024 በፓሪስ እንደሚካሄድ ከዓለም አቀፉ የኦሊምፒክ ኮሚቴ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም