ስፖርት
በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የግማሽ ፍጻሜ የባርሴሎና እና ኢንተር ሚላን ፍልሚያ
Apr 30, 2025 78
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፡- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሁለተኛ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ባርሴሎና እና ኢንተር ሚላን ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 4 ሰዓት ላይ በካምፕኑ ስታዲየም ይካሄዳል። በሩብ ፍጻሜው ባርሴሎና ቦሩሲያ ዶርትሙንድን፣ ኢንተር ሚላን ባየር ሙኒክን በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜው ደርሰዋል። ሁለቱ ክለቦች በውድድሩ በግማሽ ፍጻሜ ደረጃ ሲገናኙ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ ነው። እ.አ.አ 2009/10 ኢንተር ሚላን በደርሶ መልስ ውጤት 3 ለ 2 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። ኔራዙሪዎቹ በፍጻሜው ባየር ሙኒክን በማሸነፍ ዋንጫውን ማንሳታቸው አይዘነጋም። በአጠቃላይ ሁለቱ ክለቦች በሻምፒዮንስ ሊጉ 12 ጊዜ ተገናኝተው ባርሴሎና 6 ጊዜ ሲያሸንፍ ኢንተር ሚላን ያሸነፈው 2 ጊዜ ብቻ ነው። 4 ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። ባርሴሎና ሻምፒዮንስ ሊጉን 5 ጊዜ፣ ኢንተር ሚላን ደግሞ 3 ጊዜ ማንሳት ችለዋል። በውድድሩ ለረጅም ጊዜ የካበተ ልምድ ያላቸው ሁለቱ ክለቦች የሚያደርጉት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የ42 ዓመቱ ፈረንሳዊ ክሌመንት ቱርፓን ጨዋታውን በመሐል ዳኝነት ይመሩታል። ትናንት በሻምፒዮንስ ሊጉ በተደረገ የመጀመሪያ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ፒኤስጂ ከሜዳው ውጪ አርሰናልን 1 ለ 0 አሸንፏል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ይጀመራል 
Apr 30, 2025 55
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 22/2017(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ። ስሑል ሽሬ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 9 ሰዓት፣ አዳማ ከተማ ከወልዋሎ አዲግራት ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ይጫወታሉ። መርሃ ግብሩ ነገም ቀጥሎ ሲውል ኢትዮጵያ ቡና ከድሬዳዋ ከተማ፣ ፋሲል ከነማ ከሀድያ ሆሳዕና እና መቀሌ 70 እንደርታ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የ27ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ሚያዚያ 25 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚቆይ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል። ኢትዮጵያ መድን ሊጉን በ51 ነጥብ እየመራ ሲሆን ባህር ዳር ከተማ በ40 ነጥብ ይከተላል። ኢትዮጵያ ቡና በ39 እና መቻል በ38 ነጥብ ሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃን ይዘዋል። ሃዋሳ ከተማ፣ አዳማ ከተማ፣ ስሑል ሽሬ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከ15ኛ እስከ 18ኛ ያለውን ደረጃ በመያዝ ወራጅ ቀጠና ላይ ይገኛሉ። የሃዋሳ ከተማው ዓሊ ሱሌይማን በ12 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። የኢትዮጵያ መድኑ መሐመድ አበራ፣ የመቻል ሽመልስ በቀለ እና የአርባምንጭ ከተማው አህመድ ሁሴን በተመሳሳይ 10 ጎሎችን በማስቆጠር ይከተላሉ።
የዓለም የእግር ኳስ አፍቃሪያን ዓይኖች ሁሉ ወደ ኤምሬትስ ያማትራሉ
Apr 29, 2025 101
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 21/2017 (ኢዜአ)፡- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር አርሰናል እና ፒኤስጂ ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ የተመልካቾችን ቀልብ አርፎበታል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 4 ሰዓት ላይ በኤምሬትስ ይካሄዳል። በሩብ ፍጻሜው አርሰናል የ15 ጊዜ የውድድሩን አሸናፊ ሪያል ማድሪድን በድንቅ ብቃት በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ተጋጣሚው ፒኤስጂ በበኩሉ በአስቶንቪላ ቢፈተንም የመጨረሻ አራት ውስጥ ገብቷል። ሁለቱ ቡድኖች በመስከረም ወር 2017 ዓ.ም በሻምፒዮንስ ሊጉ ተገናኝተው አርሰናል በቡካዮ ሳካ እና ካይ ሃቫርትዝ ግቦች 2 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ቡድኖቹ እ.አ.አ 2016/17 በምድብ ደረጃ ተገናኝተው ሁለት ጊዜ ሳይሸናነፉ አቻ ተለያይተዋል። የለንደን እና የፓሪስ ከተማ ክለቦቹ በዛሬው ጨዋታ ተመጣጣኝ እና ለተመልካች አዝናኝ ፉክክር ያሳያሉ ተብሎ ይጠበቃል። የ45 ዓመቱ ስሎቬኒያዊ ስላቫኮ ቪንቺች ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌላኛው የግማሽ ፍጻሜ መርሃ ግብር ባርሴሎና ከኢንተር ሚላን ነገ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው።
ናፖሊ የሊጉን መሪነት ከኢንተር ሚላን ተረከበ
Apr 27, 2025 107
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017 (ኢዜአ)፦ በጣልያን ሴሪአ የ34ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ ሰባት ጨዋታዎች ተደርገዋል። የዋንጫ ተፎካካሪዎቹ ኢንተር ሚላን እና ናፓሊ ጨዋታቸውን አካሂደዋል። በሳንሲሮ ስታዲየም ኢንተር ሚላን ሮማን አስተናግዶ 1 ለ 0 ተሸንፏል። አርጀንቲናዊው ማቲያስ ሱሌ የማሸነፊያ ግቧን አስቆጥሯል። በዲያጎ አርማንዶ ማራዶና ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ናፖሊ ቶሪኖን 2 ለ 0 አሸንፏል። ስኮት ማክቶሚናይ ሁለቱንም ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቶቹን ተከትሎ ናፖሊ በ74 ነጥብ የሊጉን መሪነት ከኢንተር ሚላን ተረክቧል። ኢንተር ሚላን በ71 ነጥብ ወደ ሁለተኛ ደረጃ ዝቅ ብሏል። የአራት ሳምንት መርሃ ግብር የቀረው የጣልያን ሴሪአ ዋንጫውን ማን ያነሳል? የሚለው ጉዳይ ይበልጥ አጓጊ ሆኗል። በሌሎች ጨዋታዎች ጁቬንቱስ ሞንዛን፣ ኤሲ ሚላን ቬኔዚያን በተመሳሳይ 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ፊዮረንቲና ኢምፖሊን 2 ለ 1 እንዲሁም ኮሞ ጄኖዋን 1 ለ 0 ሲያሸንፉ አትላንታ ከሊቼ አንድ አቻ ተለያይተዋል።
የህብረቱ አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር የሀገራቱን ሁለንተናዊ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ ነው - ኮሚሽነር ጀኔራል ደመላሽ ገብረሚካዔል
Apr 27, 2025 119
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር ከውድድርነት ባለፈ የሀገራቱን ሰላምና ሁለንተናዊ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ መሆኑን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀኔራል ደመላሽ ገብረሚካዔል ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ የተመሰረተበትን 116ኛ ዓመት በማስመልከት አምስተኛው የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር የመክፈቻ መርሃ ግብር በሻምበል አበበ ቢቂላ ስታዲየም ተካሂዷል። የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጀኔራል ደመላሽ ገብረሚካዔል በዚሁ ወቅት፤ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ባለፉት የለውጥ አመታት በርካታ የሪፎርም ስራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል ብለዋል፡፡ ሪፎርሙን ተከትሎ በሰው ሐብት ልማት፣ በቴክኖሎጂ፣ በሎጀስቲክስ፣ በምርመራ፣ በወንጀል መከላከልና በግንኙነት ዘርፎች አመርቂ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚህም የሀገራችን አስተማማኝ ሰላምና ደህንነት ማረጋገጥ መቻሉን ነው የገለጹት፡፡ ኮሚሽነር ጀኔራል ደመላሽ ገብረሚካዔል በውድድሩ ኢትዮጵያን ጨምሮ ኬንያ፣ ሩንዳ፣ ዩጋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ ደቡብ ሱዳንና ጅቡቲ ተሳታፊ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡   የውድድሩ ዋና አላማ የሀገራቱን ግንኙነት ይበልጥ በማጠናከር የምስራቅ አፍሪካን ሰላምና ደህንነት በትብብርና በቅንጅት ለማስከበር መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ወንድማማችነትን የማጠናከር፣ የእርስ በእርስ ልምድ ለመለዋወጥና ተተኪ ስፖርተኞችን የማፍራት አላማ እንዳለውም ተናግረዋል፡፡ የ116ኛውን ብሔራዊ የፖሊስ በዓል አሁን ላይ በደረስንበትን ስኬት ሳንዘናጋ ለቀጣይ ተልዕኮ የምንዘጋጅበት ነው ብለዋል፡፡   በኬንያ ናይሮቢ የኢንተርፖል ቀጣናዊ ቢሮ ተወካይ ቦስኮ ጋሂጂ፥ በበኩላቸው፤ ዛሬ የተጀመረው ስፖርታዊ ውድድር ከስፖርት ጨዋታነት ባለፈ ቀጣናዊ ትስስርን በማጎልበት የተደራጁ ወንጀለኞችንና ሽብርተኝነትን ለመከላከል ጉልህ ድርሻ ያለው ነው ብለዋል፡፡ በመሆኑም በቀጣይ የቀጣናውን ሀገራት ሁለንተናዊ ትስስር በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ላይ በጋራና በትብብር መስራት እንደሚገባ ነው የተናገሩት፡፡ 5ኛው የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት ስፖርታዊ ውድድር እስከ ሚያዚያ 25 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ይካሄዳል።
ኢትዮጵያ በሴቶች 1ሺህ 500 ሜትር የሩጫ ውድድር ሁሉንም ሜዳሊያዎች አሸነፈች
Apr 27, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ በ5ኛው የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅት ስፖርታዊ ውድድር ኢትዮጵያ በሴቶች 1ሺህ 500 ሜትር የሩጫ ውድድር ሁሉንም ሜዳሊያዎች አሸነፈች። የኢትዮጵያ ፖሊስ የተመሰረተበትን 116ኛ ዓመት በዓል በማስመልከት 5ኛው የምስራቅ አፍሪካ የፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር የመክፈቻ መርሃ ግብር ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተከናውኗል።   በመክፈቻ መርሃ ግብሩ የሴቶች 1ሺህ 500 ሜትር እና የወንዶች የ400 ሜትር የዱላ ቅብብል የሩጫ ውድድር ተካሂዷል። በሴቶች 1ሺህ 500 ሜትር የሩጫ ውድድር ኢትዮጵያውያኑ ወርቅነሽ መሰለ፣ የኔነሽ ሺመክት እና ማተቤ ፍቃዱ በቅደም ተከተል ከ1ኛ እስከ 3ኛ በመውጣት ሁሉንም ሜዳሊያዎች ወስደዋል። በወንዶች የ400 ሜትር የዱላ ቅብብል ውድድር ደግሞ ኬንያ አንደኛ ኢትዮጵያ ሁለተኛ እንዲሁም ታንዛኒያ ሶስትኛ በመውጣት ውድድሩን አሸንፈዋል።   አሸናፊዎቹ አትሌቶች የሜዳሊያ ሽልማታቸውን ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ እጅ ተቀብለዋል። ኢትዮጵያን ጨምሮ ሰባት ሀገራት የሚሳተፉበት 5ኛው የምስራቅ አፍሪካ የፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር እስከ ሚያዚያ 25/2017 ዓ.ም ድረስ ይቀጥላል።
ሞገስ ጥዑማይ እና ገመኔ ማሚቴ የኢትዮጵያ ታምርት የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር አሸናፊ ሆኑ
Apr 27, 2025 58
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድርን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ክለብ ሞገስ ጥዑማይ በወንዶች እንዲሁም የኮዬ ፈጬ ክፍለ ከተማዋ ገመኔ ማሚቴ በሴቶች አሸናፊ ሆነዋል። መነሻና መድረሻውን በመስቀል አደባባይ ያደረገው 4ኛ ዓመት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የ2017 ኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ የ10 ኪ.ሜ የጎዳና ላይ የሩጫ ውድድር ተካሂዷል። በዝግጅቱ ላይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን(ዶ/ር)፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ጃንጥራር ዓባይን ጨምሮ የፌዴራልና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በውድድሩም የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ክለብ ሞገስ ጥዑማይ በወንዶች እንዲሁም የኮዬ ፈጬ ክፍለ ከተማዋ ገመኔ ማሚቴ በሴቶች የኢትዮጵያ ታምርት የ10 ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር አሸነፊ ሆነዋል። በዚህም በ10 ኪሎ ሜትር የኢትዮጵያ ታምርት የወንዶች የሩጫ ውድድር፦ 1ኛ. ሞገስ ጥዑማይ ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ የወርቅ ሜዳሊያ እና የ300 ሺህ ብር፣ 2ኛ.ጅራታ ሌሊሳ በግል የብር ሜዳሊያና የ200 ሺህ ብር እንዲሁም 3ኛ. ሲዳ አማና ከሸገር ከተማ የነሀስ ሜዳሊያ እና የ100 ሺህ ብር ሽልማት አሸናፊ በመሆን ከኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል እና ከኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡሉልታ እጅ የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ተረክበዋል።   በተመሳሳይ በ10 ኪሎ ሜትር የኢትዮጵያ ታምርት የሴቶች የሩጫ ውድድር፦ 1ኛ. ገመኔ ማሚቴ ከኮዬ ፈጬ ክፍለ ከተማ የወርቅ ሜዳሊያ እና የ300 ሺህ ብር፤ 2ኛ.አበዙ ከበደ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የብር ሜዳሊያና የ200 ሺህ ብር እንዲሁም፤ 3ኛ. ማርታ አለማየሁ በግል የነሀስ ሜዳሊያ እና የ100 ሺህ ብር አሸናፊ በመሆን ከባህልና ስፖርት ሚኒስትር ሸዊት ሻንካ እና ከአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ጃንጥራር ዓባይ ዕጅ የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ተረክበዋል። የሩጫ ውድድሩን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ሲሆን ውድድሩም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 4ኛ ዓመት ዝግጅትን አስመልክቶ የተሰናዳ መሆኑ ተገልጿል።
ተጠባቂው የለንደን ማራቶን
Apr 27, 2025 53
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2017 (ኢዜአ)፡- 45ኛው የለንደን ማራቶን ዛሬ ረፋድ ላይ ይካሄዳል። በሁለቱም ጾታዎች የሚደረጉ የዓለም የአትሌቲክስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። በሴቶች አትሌት ትዕግስት አሰፋ እና አትሌት ሲፋን ሀሰን የሚያደርጉት ፉክክር በጉጉት እንደሚጠበቅ የዓለም አትሌቲክስ መረጃ ያመለክታል። ሁለቱ አትሌቶች በፓሪስ በተካሄደው 33ኛው የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በማራቶን ውድድር እስከ መጨረሻው እልህ አስጨራስ ፉክክር አድርገው ሲፋን አንደኛ፣ ትዕግስት ሁለተኛ ደረጃን ይዘው ማጠናቀቃቸው የሚታወስ ነው። አትሌቶቹ ከኦሊምፒኩ መልስ ዳግም በወሳኝ የአትሌቲክስ መድረግ ላይ ተገናኝተዋል። አትሌት ትዕግስት 2 ሰዓት ከ11 ደቂቃ ከ53 ሴኮንድ በርቀቱ የዓለም ሁለተኛ ፈጣን ሰዓት ባለቤት ናት። ሲፋን 2 ሰዓት ከ13 ደቂቃ ከ44 ሴኮንድ የዓለም ሶስተኛ ፈጣን ሰዓትን አስመዝግባለች።   ኬንያዊቷ የማራቶን የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት ሩት ቼፕጌቲች እና የባለፈው ዓመት የውድድሩ አሸናፊ የሆነችው ሌላኛዋ ኬንያዊ አትሌት ፔሬዝ ቼፕቺርቺር በውድድሩ ላይ አይሳተፉም። ሌላኛዋ ኬንያዊ ጆይስሊን ጄፕኮስጌ የሀገሬው ሰዎች ተስፋ የጣሉበት አትሌት ናት። በወንዶች በፓሪስ የኦሊምፒክ ጨዋታዎች በማራቶን የወርቅ ሜዳሊያ ያገኘው አትሌት ታምራት ቶላ እንዲሁም ኬንያዊው ኢሊውድ ኪፕቾጌ እና ሌላኛው የሀገሩ ልጅ አሌክሳንዳር ሙቲሶ ሙናዮ የማሸነፉን የቅድሚያ ግምት አግኝተዋል። ሙናዮ የባለፈው ዓመት የውድድሩ አሸናፊ ነው።   ዩጋንዳዊው ጃኮብ ኪፕሊሞ ሌላኛው ተጠባቂ አትሌት ነው። አንጋፋው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ በጉዳት ምክንያት ከውድድሩ ውጪ መሆኑ የሚታወስ ነው። በሁለቱም ጾታዎች የሚያሸንፉ አትሌቶች በተመሳሳይ የ55 ሺህ የአሜሪካን ዶላር ሽልማት ያገኛሉ። እ.አ.አ በ1981 የተጀመረው የለንደን ማራቶን በዓለም አትሌቲክስ የወርቅ ደረጃ የተሰጠው የጎዳና ላይ ውድድር ሲሆን በዓለም ላይ ተጠባቂ ከሆኑ ውድድሮች መካከል በዋናነት የሚጠቀስ ነው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም