ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
በያዝነው ወር ሶስት ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ኩነቶች አዲስ አበባ ይካሄዳሉ
Apr 16, 2026 161
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 8/2018(ኢዜአ)፦ዓለም አቀፉ አዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአትሌቲክስ ውድድርን ጨምሮ አዲስ አበባ ውስጥ በሚያዚያ ወር ሶስት ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ኩነቶች ይካሄዳሉ። ከሚካሄዱት ዓለምአቀፍ ስፖርታዊ ኩነቶች ውስጥ አንዱ የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአንድ ቀን የአትሌቲክስ ውድድር በመጪው ቅዳሜ ይካሄዳል። ይህ ውድድር በአዲስ አበባ ሲካሄድ የመጀመሪያው ሲሆን መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት የስፖርት መሰረተ ልማቶች መስፋፋት ምቹ ሆኔታ መፍጠሩ ነው የተገለፀው። በአዲስ አበባ ስታዲዮም በሚካሄደው ውድድር ላይ በዓለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ እና ብዙ ተከታይ ያላቸው አትሌቶች ይሳተፉበታል ተብሏል። ሲቲ ማውንቴን ባይክ ኢሊሚኔተር ዓለም አቀፍ የብስክሌት ውድድር እና ግራንድ ኢትዮጵያን ረን ሚያዝያ ውስጥ የሚካሄዱ ውድድሮች ናቸው። ከተማ አስተዳደሩ ውድድሩን ለማሳካት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቂ ዝግጅቶች ከማድረግ በዘለለ በኢትዮጵያ ያሉትን የስፖርት መሰረተ ልማቶች ለማስተዋወቅ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ ተመልክቷል።
ባየር ሙኒክ እና አርሰናል ለግማሽ ፍጻሜ አለፉ
Apr 16, 2026 239
አዲስን አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ቀሪ ሁለት የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። በአሊያንዝ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በመደበኛው ክፍለ ጊዜ ባየር ሙኒክ ሪያል ማድሪድን 4 ለ 3 አሸንፏል። አሌክሳንደር ፓቭሎቪች፣ ሃሪ ኬን፣ሉዊስ ዲያዝ እና ማይክል ኦሊሴ ለባየር ሙኒክ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። አርዳ ጉለር ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ኪሊያን ምባፔ ቀሪዋን ጎል ለማድሪድ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ተቀይሮ የገባው ኤድዋርዶ ካማቪንጋ በ86ኛው ደቂቃ በሁለት ቢጫ በቀይ ካርድ ወጥቷል። ከቀይ ካርዱ በኋላ ሙኒክ ሁለት ግቦችን አስቆጥሯል። በጨዋታው ባለሜዳው ባየር ሙኒክ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስድም ሪያል ማድሪድ በመልሶ ማጥቃት የተሻሉ የግብ እድሎች ፈጥሯል። ከጨዋታው መጠናቀቅ በኋላ አርዳ ጉለር ዳኛ በመናገሩ በቀይ ካርድ ወጥቷል። ባየር ሙኒክ በድምር ውጤት 6 ለ 4 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። በሌላኛው መርሐ ግብር አርሰናል እና ስፖርቲንግ ሊዝበን ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። በኤምሬትስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በቂ የግብ እድሎች የተፈጠሩበት አልነበረም። ውጤቱን ተከትሎ አርሰናል በድምር ውጤት 1 ለ ዐ በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ተጠናቋል። በግማሽ ፍጻሜው ባየር ሙኒክ ከፒኤስጂ የሚያደርጉት ጨዋታ ከወዲሁ በጉጉት ይጠበቃል። አርሰናል በግማሽ ፍጻሜው ከአትሌቲኮ ማድሪድ ጋር ይገናኛል። የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሚያዚያ ወር መጨረሻ ይደረጋሉ።
መቻል ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ አደረገ
Apr 15, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መቻል ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ፤ መሐመድ ኑር ናስር በስድስተኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ድሬዳዋ መሪ ሆኗል። ዓለምብርሃን ይግዛው በ15ኛው እና ጋናዊው ኮሊንስ ኮፊ በ40ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፏቸው ግቦች መቻልን አሸናፊ አድርገዋል። የመቻሉ አማካይ ተጫዋች አብዱልከሪም ወርቁ በመጀመሪያው አጋማሽ ቡድኑ ያገኘውን የፍጹም ቅጣት ምት ሳይጠቀምበት ቀርቷል። በሊጉ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው መቻል በ43 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ32 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ ጨዋታዎች ኢትዮጵያ መድን እና ባህር ዳር ከተማ አንድ አቻ ሲለያዩ፤ ሐዋሳ ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ያካሄዱት ጨዋታ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 27ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የ28ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከሚያዝያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም አጀምሮ ይካሄዳል።
ሀላባ ከተማ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አደገ
Apr 15, 2026 208
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የ2018 የውድድር ዘመን ምድብ ለ 20ኛ ሳምንት ወሳኝ ጨዋታ ዛሬ በሀላባ ከተማ እና ደሴ ከተማ መካከል ሀዋሳ ላይ ተካሂዷል። በጨዋታውም ሀላባ ከተማ ደሴ ከተማን 1 ለ 0 በማሸነፍ ነጥቡን 38 አድርሷል። ይህም አንድ ጨዋታ እየቀረው በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ 2019 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ማደጉን እንዲያረጋግጥ ማስቻሉን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የ2018 የውድድር ዘመን በምድብ ሀ መሪ ሆኖ ያጠናቀቀው ጋሞ ጨንቻ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ማደጉ ይታወቃል። የፌዴሬሽኑ መረጃ እንደሚያመለክተው፤ ሁለት ክለቦች ወደ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሲያድጉ አራት ክለቦች ደግሞ ከሊጉ የሚወርዱ ይሆናል።
ሃዋሳ ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ነጥብ ተጋሩ
Apr 15, 2026 116
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት ሃዋሳ ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተደርጓል። ውጤቱን ተከትሎ ሃዋሳ ከተማ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከአራተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። ቡድኑ ባለፉት አራት የሊጉ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥሏል። ምድረ ገነት ሽሬ በ29 ነጥብ ደረጃውን ከ18ኛ ወደ 17ኛ ከፍ ቢያደርግም አሁንም ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊጉ ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን እና ባህር ዳር ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። አማኑኤል ኤርቦ በ41ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ግብ መድን መሪ ሆኗል። አደም አባስ በ96ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋት ጎል ለባህር ዳር ከተማ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን በ30 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ባህር ዳር ከተማ በ36 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በርካታ ጊዜ (በ15 ጨዋታዎች ) አቻ የወጣ ቡድን ነው።
በዓለም አትሌቲክስ ግራንድ ፕሪ የሚሳተፉ አትሌቶች በአዲስ አበባ ስታዲየም ልምምድ ጀመሩ
Apr 15, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7 /2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም አትሌቲክስ አዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአንድ ቀን ውድድር ተሳታፊ አትሌቶች በአዲስ አበባ ስታዲየም ዛሬ ልምምድ ማድረግ ጀምረዋል። የአዲስ አበባ ስታዲየም ከስምንት ዓመት በኋላ የመሮጫ ትራክ እድሳቱ ተጠናቅቆ ዛሬ በአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ ዓለም አቀፍ ውድድር ለሚሳተፉ አትሌቶች ክፍት ሆኗል። ባለፉት ዓመታት በእድሳት ምክንያት ከአገልግሎት ውጪ የነበረው ስታዲየሙ፣ በአዲስ መልክ እድሳት ተደርጎለት አሁን ለውድድርና ለልምምድ ዝግጁ መሆኑን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ቅዳሜ ሚያዚያ 10 የሚደረገውን የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአንድ ቀን ውድድር ስኬታማ እንዲሆን፣ የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የመሮጫ መም እድሳቱን በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጠናቀቅ ላደረገው ርብርብ ፌዴሬሽኑ ምስጋናውን አቅርቧል። ሚኒስቴሩ ለኢትዮጵያ አትሌቲክስ እድገትና ልማት የሰጠው ልዩ ትኩረት ለስፖርቱ መነቃቃት የማይተካ ሚና እንዳለው በመረጃው ላይ ተመላክቷል። የዓለም አትሌቲክስ ዓመታዊ አህጉራዊ ውድድር አካል የሆነው አዲስ አበባ ግራንድ ፕሪ የአንድ ቀን ውድድር በኢትዮጵያ ሲካሄድ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።
ሃዋሳ ከተማ ከምድረ ገነት ሽሬ መቻል ከድሬዳዋ ከተማ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ዛሬ ይጠበቃሉ
Apr 15, 2026 117
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ሃዋሳ ከተማ ከምድረ ገነት ሽሬ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሃዋሳ ከተማ በውድድር ዓመቱ 26 ጨዋታዎችን አድርጎ በ11ዱ ሲያሸንፍ በሰባቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ስምንት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። 30 ግቦችን በ26ቱ ጨዋታዎች ላይ ሲያስቆጥር 21 ጎሎችን አስተናግዷል። ሃዋሳ ከተማ በ41 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ካከናወናቸው 26 ጨዋታዎች መካከል ስድስቱን ያሸነፈው ምድረ ገነት ሽሬ በበኩሉ 10 ጊዜ ተሸንፏል። 10 ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 17 ግቦችን ሲያገባ 21 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ምድረ ገነት ሽሬ በ28 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ባለፉት ሶስት የሊጉ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ ማሸነፍ በዋንጫ ፉክክሩ ለመቆየት የሚያስችለውን ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያገኛል። ደረጃውን ወደ ሁለተኛ ከፍ ያደርጋል። ካለፉት አምስት የሊጉ ጨዋታዎች አንዱንም ማሸነፍ ያልቻለው ምድረ ገነት ሽሬ ሶስት ነጥብ ማግኘት ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ጥረት ወሳኝ የሚባል ነው። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በዝናብ ምክንያት ሳይካሄድ ቀርቶ ከሚያዚያ 5 ወደ ዛሬ የተሸጋገረ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ድሬዳዋ ከተማ ከመቻል በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ድሬዳዋ ከተማ በሊጉ ካደረጋቸው 26 ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ሲያሸንፍ ስምንት ጊዜ ተሸንፏል። 11 ጊዜ አቻ ተለያይቷል። 18 ግቦችን በጨዋታዎቹ ላይ ሲያስቆጥር 25 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ32 ነጥብ 14ተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በበኩሉ በውድድር ዓመቱ 26 ጨዋታዎችን አድርጎ በ10ሩ ድል ሲቀናው ስድስት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ 10 ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። 33 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 21 ግቦች ተቆጥረውበታል። መቻል በ40 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ26ኛ ሳምንት ድሬዳዋ ከተማ ምድረ ገነት ሽሬን 1 ለ 0፣ መቻል የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡናን 3 ለ 1 አሸንፈዋል። ሁለቱም ቡድኖች በድል ጉዟቸው ለመቀጠል ይፋለማሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ መድን ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ መድን በሊጉ ባካሄዳቸው 26 ጨዋታዎች ስድስት ጊዜ ሲያሸንፍ ዘጠኝ ጊዜ ተሸንፏል። በ11 ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 20 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ በተመሳሳይ 20 ጎሎች ተቆጥረውበታል። መድን በ29 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ባህር ዳር ከተማ በበኩሉ ከ26 የሊጉ ጨዋታዎች መካከል ሰባቱን ሲያሸንፍ በአምስቱ ሽንፈት አጋጥሞታል። በ14 ጨዋታዎች ደግሞ አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 19 ግቦች ሲያስቆጥር 18 ግቦችን አስተናግዷል። ባህር ዳር ከተማ በ35 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ድል ያልቀናው የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ስጋት በመጠኑ እንዲርቅ ያስችለዋል። በ26ኛ ሳምንት አዳማ ከተማን 2 ለ 1 የረታው ባህር ዳር ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በርካታ ጊዜ (በ14 ጨዋታዎች ) አቻ የወጣ ቡድን ነው።
የባየር ሙኒክ እና የሪያል ማድሪድ ተጠባቂ የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታ
Apr 15, 2026 254
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ቀሪ ሁለት የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ዛሬ ማምሻውን ይካሄዳሉ። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ባየር ሙኒክ ከሪያል ማድሪድ 75 ሺህ 24 ተመልካቾችን በሚያስተናግደው አሊያንዝ አሬና ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ሁለቱ ቡድኖች ባለፈው ሳምንት በበርናባው ባካሄዱት ጨዋታ ባየር ሙኒክ 2 ለ 1 አሸንፏል። ሉዊስ ዲያዝ እና ሃሪ ኬን የማሸነፊያ ግቦቹን ያስቆጠሩ ተጫዋቾች ናቸው። ኪሊያን ምባፔ ለማድሪድ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱ ባየር ሙኒክ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ ያለውን እድል የተሻለ አድርጓል። የ15 ጊዜ የዋንጫው ባለቤት ሪያል ማድሪድ ወደ ግማሽ ፍጻሜ የመግባት እድሉ ያበቃለት አይደለም። በሻምፒዮንስ ሊጉ ላይ ትኩረቱን ያደረገው ማድሪድ ውጤቱን ለመቀልበስ ጠንካራውን ባየር ሙኒክ ማሸነፍ ይጠበቅበታል። የስድስት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ባየር ሙኒክ፣ ወደ ግማሽ ፍፃሜው (አራት ውስጥ) የመግባት ዕድሉ በራሱ እጅ ላይ ይገኛል። በሌላኛው መርሐ ግብር አርሰናል ስፖርቲንግ ሊዝበንን ምሽት አራት ሰዓት ላይ በኤምሬትስ ስታዲየም ያስተናግዳል። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ጨዋታ አርሰናል ከሜዳው ውጪ በካይ ሃቫርትዝ ጎል 1 ለ 0 አሸንፏል። አርሰናል ወደ ግማሽ ፍጻሜ የመግባት ሰፊ ግምት አግኝቷል። የፖርቹጋሉ ስፖርቲንግ ሊዝበን ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ በውድድሩ ጠንካራ ቡድን የሆነውን አርሰናልን ከሜዳው ውጪ የማሸነፍ ከባድ የቤት ስራ ይጠብቀዋል። ትናንት በተደረጉ የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ፒኤስጂ ሊቨርፑልን፣ አትሌቲኮ ማድሪድ ባርሴሎናን በድምር ውጤት በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፈዋል።
ፒኤስጂ እና አትሌቲኮ ማድሪድ ለግማሽ ፍጻሜ አለፉ
Apr 15, 2026 194
አዲስን አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ሁለት የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ማምሻውን ተደርገዋል። በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፒኤስጂ ሊቨርፑልን 2 ለ 0 አሸንፏል። ኡስማን ዴምቤሌ በ72ኛው እና 91ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎሎቹን አስቆጥሯል። የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ በድምር ውጤት 4 ለ 0 በማሸነፍ ለግማሽ ፍጻሜ አልፏል። ፒኤስጂ በግማሽ ፍጻሜው ከባየር ሙኒክ እና ሪያል ማድሪድ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ባርሴሎና አትሌቲኮ ማድሪድን 2 ለ 1 አሸንፏል። በዋንዳ ሜትሮፖሊታኖ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ላሚን ያማል እና ፌራን ቶሬስ ለባርሴሎና ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አዴሞላ ሉክማን ለአትሌቲኮ ማድሪድ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። የባርሴሎናው ኤሪክ ጋርሺያ በ80ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በመጀመሪያው ጨዋታም የባርሴሎናው ፓው ኩባርሲ በቀይ ካርድ መውጣቱ የሚታወስ ነው። በጨዋታው ባርሴሎና ብልጫ ቢወስድም ጨዋታውን ለመቀልበስ የሚያስችሉ ተጨማሪ ጎሎችን ማስቆጠር አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ አትሌቲኮ ማድሪድ በድምር ውጤት 3 ለ 2 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። የማድሪዱ ክለብ በግማሽ ፍጻሜው ከአርሰናል እና ስፖርቲንግ ሊዝበን አሸናፊ ጋር ይጫወታል። የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር ነገም ሲቀጥል ባየር ሙኒክ ከሪያል ማድሪድ እና አርሰናል ከስፖርቲንግ ሊዝበን ይጫወታሉ።
ፋሲል ከነማ ደረጃውን ወደ ሶስተኛ ከፍ አደረገ
Apr 14, 2026 274
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ፋሲል ከነማ ወላይታ ድቻን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ታምራት እያሱ በ20ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ታምራት በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ዘጠኝ አድርሷል። ውጤቱን ተከትሎ በሊጉ 10ኛ ድሉን ያስመዘገበው ፋሲል ከነማ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ ሶስተኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ወላይታ ድቻ በ31 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ27ኛ ሳምንት ጨዋታዎች የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ አዳማ ከተማን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ሀድያ ሆሳዕና እና ኢትዮጵያ ቡና ሁለት አቻ ተለያይተዋል።
የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ለፍጻሜ ሳይደርስ ቀረ
Apr 14, 2026 101
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በ"UEFA Frendship Cup" ከ18 ዓመት በታች ሴቶች መርሐ ግብር ኖርዌይ ኢትዮጵያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። የሁለቱ ሀገራት የምድብ ሁለት ጨዋታ በቱርኪዬ ሪቫ ስታዲየም ተደርጓል። ውጤቱን ተከትሎ የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ለፍጻሜ ማለፍ ሳይችል ቀርቷል። ኖርዌይ በዘጠኝ ነጥብ ለፍጻሜ አልፋለች። በተያያዘም በምድብ አንድ በተደረጉ ጨዋታዎች ፓራጓይ ኡዝቤኪስታንነ 7 ለ 0 ስትረታ፣ ቱርኪዬ ሞሮኮን በመለያ ምት አሸንፋለች። ፓራጓይ በስድስት ነጥብ ተመሳሳይ ነጥብ ያላትን ቱርኪዬ በግብ ክፍያ በልጣ ለፍጻሜ አልፋለች። ኖርዌይ ከፓራጓይ የፍጻሜው ጨዋታቸውን ሚያዚያ 9 ቀን 2018 ዓ.ም በሪቫ ስታዲየም ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ ሶስተኛ ደረጃን ለማግኘት ከቱርኪዬ ጋር በዕለቱ ትፋለማለች። የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ያዘጋጀው የወዳጅነት ዋንጫ ከውድድር ባለፈ የክፍለ አህጉራዊ እግር ኳስ ልማት ትብብርን ማጠናከርን ያለመ ነው።
ሀድያ ሆሳዕና እና ኢትዮጵያ ቡና ነጥብ ተጋሩ
Apr 14, 2026 115
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት መርሀግብር ሀድያ ሆሳዕና እና ኢትዮጵያ ቡና ሁለት አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ እዮብ አለማየሁ እና ብሩክ በየነ የሀድያ ሆሳዕናን ግቦች አስቆጥረዋል። ዘላለም አባተ እና ራምኬል ጀምስ ለኢትዮጵያ ቡና ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ላይ ኢትዮጵያ ቡና ሁለት ጊዜ ቢመራም ውጤቱን ማስጠበቅ አልቻለም። ሀድያ ሆሳዕና በ33 ነጥብ ደረጃውን ከ13ኛ ወደ 11ኛ ከፍ አድርጓል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ በ37 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።
ሲዳማ ቡና መሪነቱን ያጠናከረበት ድል ተቀዳጀ
Apr 14, 2026 103
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 1 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አቤል ያለው በመጀመሪያው አጋማሽ ማብቂያ ላይ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ሲዳማ ቡና ነጥቡን ወደ 51 ከፍ በማድረግ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ ነገሌ አርሲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ስምንት ከፍ አድርጓል። ቡድኑ በአጠቃላይ በውድድር ዓመቱ ያሸነፋቸው ጨዋታዎች ብዛት 14 ደርሰዋል። በሊጉ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ34 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Apr 14, 2026 122
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ አዳማ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ያሬድ የማነ በ43ኛው ደቂቃ ግቧን አስቆጥሯል። ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ41 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አራተኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ያሸነፋቸውን የጨዋታዎች ብዛት ወደ 10 አድርሷል። በአንጻሩ በሊጉ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።
ኢትዮጵያ በዩኤፋ ወዳኝነት ዋንጫ ለፍጻሜ ለማለፍ ከኖርዌይ ጋር ዛሬ የምታደርገው ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Apr 14, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ያዘጋጀው የ"UEFA Frendship Cup" ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ውድድር በቱርክዬ በመካሄድ ላይ ይገኛል። በውድድሩ ላይ ተሳታፊ የሆነው የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን የምድብ ሁለት የመጨረሻ ጨዋታውን ከኖርዌይ ጋር ዛሬ ከቀኑ 10 ሰዓት ከ30 ላይ ያደርጋል። በቻለው ለሜቻ የሚመራው ብሔራዊ ቡድኑ በምድቡ ባደረጋቸው ጨዋታዎች ዩራጓይን 3 ለ 0፣ ኮስታሪካን 1 ለ 0 አሸንፏል። ቡድኑ በስድስት ነጥብ እና በአራት የግብ ክፍያ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚዋ ኖርዌይ በምድቡ ዩራጓይን 6 ለ 0 እና ኮስታሪካን 4 ለ 1 አሸንፋለች። ኖርዌይ በስድስት ነጥብ እና በዘጠኝ የግብ ክፍያ ምድቡን እየመራች ነው። ኢትዮጵያ ወደ ፍጻሜው ጨዋታ ለማለፍ የግድ ኖርዌይን ማሸነፍ ይጠበቅባታል። በአንጻሩ ኖርዌይ ማሸነፍ ወይም አቻ መውጣት ወደ ፍጻሜው ያሳልፋታል። ‘ ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። በውድድሩ ላይ ድንቅ ብቃቷን እያሳየች የምትገኘው ሕድኣት ካሱ አራቱንም የኢትዮጵያ ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፋለች። ኮስታሪካ ላይ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርታለች። በተያያዘም በምድብ አንድ ቱርክዬ ከሞሮኮ ከቀኑ 10 ሰዓት ከ30 እና ፓራጓይ ከኡዝቤኪስታን ከረፋዱ 5 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ። ሞሮኮ ምድቡን በስድስት ነጥብ ትመራለች። ፓራጓይ እና ቱርክዬ በተመሳሳይ ሶስት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል። ከምድቡ አንደኛ የሚወጣው ሀገር ወደ ፍጻሜው ያልፋል። የወዳጅነት ዋንጫው ከውድድር ባለፈ የክፍለ አህጉራዊ እግር ኳስ ልማት ትብብርን ማጠናከርን ያለመ ነው።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት የጨዋታ መርሐ ግብር ላይ ማሻሻያ ተደረገ
Apr 14, 2026 114
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ27ኛ ሳምንት የጨዋታ መርሐ ግብር ላይ መጠነኛ ማሻሻያ መደረጉን የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታወቀ። ፕሪሚየር ሊጉ ከ25ኛ ሳምንት ጀምሮ በአዲስ አበባ እና በሃዋሳ ከተሞች በድምቀት እየተካሄደ እንደሚገኝ ይታወቃል። ይሁን እንጂ የ27ኛ ሳምንት የመጀመርያ ቀን ሁለተኛ ጨዋታ የነበረው የሃዋሳ ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ግጥሚያ፣ በሃዋሳ ከተማ ባጋጠመ አስቸጋሪ የአየር ሁኔታ ምክንያት ሜዳው ለጨዋታ አመቺ ባለመሆኑ ሳይከናወን ቀርቷል። ይህንን ተከትሎ የውድድርና ስነ ስርዓት ኮሚቴ ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ፣ ሳይከናወን የቀረው የሃዋሳ ከተማ እና ምድረ ገነት ሽሬ ጨዋታ ረቡዕ ሚያዝያ 7 ቀን 2018 ዓ.ም ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ እንዲደረግ ወስኗል። በተጨማሪም በዚሁ ዕለት ሊካሄድ የነበረው የድሬዳዋ ከተማ እና መቻል ጨዋታ ወደ ምሽቱ 12 ሰዓት ተገፍቶ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም እንዲከናወን መርሐ ግብሩ ተሻሽሏል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ሚያዝያ 6 እና 7 ሊካሄዱ የታቀዱ የ27ኛ ሳምንት ጨዋታዎች፣ ተመሳሳይ የአየር ሁኔታ አጋጥሞ መጫወት ካልተቻለ ጨዋታዎቹ በቀጣዩ ቀን በተለዋጭ ሜዳ እና ሰዓት እንደሚከናወኑ የውድድርና ስነ ስርዓት ኮሚቴው አስታውቋል። አክሲዮን ማህበሩ ባስተላለፈው መረጃ መሠረት፤ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም የሚደረጉ ቀሪ የሳምንቱ ጨዋታዎች የቀረፃ ሽፋን ብቻ የሚሰጣቸው ሲሆን የቀጥታ ስርጭት ግን አይኖራቸውም።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Apr 14, 2026 158
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሲዳማ ቡና በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባደረጋቸው 26 ጨዋታዎች መካከል ስምንቱን ሲያሸንፍ በተመሳሳይ ስምንት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በ10 ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ26ቱ ጨዋታዎች ላይ 35 ጎሎችን ሲያስቆጥር 32 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ34 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና 26 ጨዋታዎችን አከናውኖ በ13ቱ አሸንፎ በአራቱ ተሸንፎ ዘጠኝ ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። በ26ኛ ሳምንት መቀሌ 70 እንደርታን 3 ለ 0 ያሸነፈው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። በአንጻሩ በ26ኛ ሳምንት በመቻል የ3 ለ 1 ሽንፈት ያስተናገደው ሲዳማ ቡና ማሸነፍ ከሽንፈቱ በማገገም የሊጉን መሪነት ለማጠናከር ያስችለዋል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ወላይታ ድቻ ከፋሲል ከነማ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ወላይታ ድቻ በውድድር ዓመቱ 26 ጨዋታዎችን አድርጎ ስድስቱን ሲያሸንፍ በሰባቱ ሽንፈት አስተናግዷል። 13 ጊዜ ደግሞ አቻ ወጥቷል። 27 ግቦችን በ26ቱ ጨዋታዎች ላይ ሲያስቆጥር 26 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ31 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በሊጉ ካከናወናቸው 26 ጨዋታዎች መካከል ዘጠኙን ያሸነፈው ፋሲል ከነማ በበኩሉ አምስት ጊዜ ተሸንፏል። 12 ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 18 ግቦችን ሲያገባ 15 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ፋሲል ከነማ በ39 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። በ26ኛ ሳምንት ወላይታ ድቻ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን፣ ፋሲል ከነማ ሃዋሳ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፈዋል። ሁለቱም ቡድኖች ተከታታይ ድላቸውን ለማስመዝገብ ይፋለማሉ። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። አዳማ ከተማ በ33 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ38 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ያላሸነፈው አዳማ ከተማ ወደ ድል መንገድ ለመመለስ ይጫወታል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ድል ያልቀናው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይፋለማል። ሀድያ ሆሳዕና ከኢትዮጵያ ቡና ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሀድያ ሆሳዕና በ32 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ኢትዮጵያ ቡና በበኩሉ በ36 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ26ኛ ሳምንት አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 ያሸነፈው ሀድያ ሆሳዕና ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይፋለማል። በአንጻሩ በ26ኛ ሳምንት ከሸገር ከተማ አንድ አቻ የተለያየው ኢትዮጵያ ቡና ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል።
የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች
Apr 14, 2026 158
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ):- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዛሬ ሁለት የሩብ ፍጻሜ የመልስ ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ምሽት አራት ሰዓት ላይ ሊቨርፑል ፒኤስጂን በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም ያስተናግዳል። ሁለቱ ቡድኖች ባለፈው ሳምንት ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ፒኤስጂ በዴዚሬ ዱዌ እና ክቪቻ ክቫራትስኬሊያ ጎሎች 2 ለ 0 አሸንፏል። ውጤቱን ተከትሎ የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ ወደ ግማሽ ፍጻሜ የመግባት እድሉን አስፍቷል። የስድስት ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል ውጤቱን የመቀልበስ ጠንካራ ፈተና ይጠብቀዋል። ሁለቱ ቡድኖች ባለፈው የውድድር ዓመት በጥሎ ማለፉ ተገናኝተው ፒኤስጂ በድምር ውጤት በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜ መግባቱ የሚታወስ ነው። ሌላኛው ጨዋታ ምሽት አራት ሰዓት ላይ አትሌቲኮ ማድሪድ እና ባርሴሎናን በዋንዳ ሜትሮፖሊታኖ ስታዲየም ያገናኛል። የስፔን ክለቦቹ በመጀመሪያው ዙር በካምፕ ኑ ስታዲየም ባከናወኑት ጨዋታ አትሌቲኮ ማድሪድ 2 ለ 0 አሸንፏል። ሁሊያን አልቫሬዝ እና አሌክሳንደር ሶርሎዝ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የማድሪዱ ክለብ ከሜዳው ውጪ ያገኘው ድል ወደ ግማሽ ፍጻሜ የመግባት እድሉን አስፍቶታል። ባርሴሎና ወደ ቀጣዩ ዙር ለማለፍ በዘንድሮው የውድድር ዓመት በሜዳው ለማሸነፍ ከባድ የሆነው አትሌቲኮ ማድሪድን ከሁለት ጎል በላይ ልዩነት ማሸነፍ ይጠበቅበታል
ማንችስተር ዩናይትድ በሊድስ ዩናይትድ ተሸነፈ
Apr 13, 2026 393
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 5/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሊድስ ዩናይትድ ማንችስተር ዩናይትድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በኦልድትራፎርድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኖሃ ኦካፎር የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። ካሲሚሮ ለዩናይትድ ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። የማንችስተር ዩናይትዱ ተከላካይ ሊሳንድሮ ማርቲኔዝ በ56ኛው ደቂቃ ላይ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። በጨዋታው ሊድስ ከዩናይትድ በተሻለ ግልጽ የግብ እድሎችን ፈጥሯል። በጨዋታው ላይ ጥሩ እንቅስቃሴ አድርጓል። የቁጥር ብልጫ የተወሰደበት ማንችስተር ዩናይትድ በሁለተኛው አጋማሽ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ያደረገው ጥረት አልተሳካም። ዩናይትድ በጨዋታው ያሳየው ብቃት የሚጠበቀውን ያህል አልነበረም። በሊጉ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ማንችስተር ዩናይትድ በ55 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ሻምፒዮንስ ሊግ ለመግባት የሚፎካከረው ዩናይትድ ከተከታዩ አስቶንቪላ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማስፋት እድል አልተሳካም። ከስድስት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሊድስ ዩናይትድ በ39 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ላለመውረድ በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በሊጉም ስምንተኛ ድሉን አሳክቷል። ሊድስ ከ24 ዓመታት በኋላ ዩናይትድን በሊጉ አሸንፏል። ጨዋታውን ተከትሎ 32ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የ33ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳሉ።
አርባምንጭ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ነጥብ ተጋሩ
Apr 13, 2026 390
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 5/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 27ኛ ሳምንት አርባምንጭ ከተማ እና ቅዱስ ጊዮርጊስ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ፍፁም ጥላሁን በ29ኛው እና ተገኑ ተሾመ በ36ኛው ደቂቃ ባስቆጠሯቸው ጎሎች ቅዱስ ጊዮርጊስ መሪ ሆኗል። ናይጄሪያዊው ጄሮም ፍሊፕ በ42ኛው እና ሴኔጋላዊው ማማዱ ሴክ በ97ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፏቸው ግቦች ለአርባምንጭ ከተማ ወሳኝ አንድ ነጥብ አስገኝተዋል። ቅዱስ ጊዮርጊስ የ2 ለ 0 ውጤቱን ማስመዝገብ አልቻለም። ውጤቱን ተከትሎ ቅዱስ ጊዮርጊስ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ32 ነጥብ ደረጃውን ከ15ኛ ወደ 12ኛ ከፍ አድርጓል። ቡድኑ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ማስመዝገብ አልቻለም። አርባምንጭ ከተማ በ23 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ተከታታይ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። በሀዋሳ ከተማ በጣለው ከባድ ዝናብ ምክንያት የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ሜዳ ውሃ በመያዙ፣ በሀዋሳ ከተማ እና በምድረ ገነት ሽሬ መካከል ሊደረግ የነበረው የምሽት 12 ሰዓት ጨዋታ በዳኞች ውሳኔ ሳይካሄድ ቀርቷል። የሊጉ አክሲዮን ማህበር የመርሐ ግብሩን አዲስ የጨዋታ ቀን እና ቦታ በቀጣይ እንደሚያሳውቅ ገልጿል። ዛሬ በተደረጉ የ27ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች መቀሌ 70 እንደርታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን 2 ለ 1 ሲረታ ሸገር ከተማ እና ነገሌ አርሲ አንድ አቻ ተለያይተዋል።