ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 26, 2026 38
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ድሬዳዋ ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአርባምንጭ ከተማዋ መድሃኒት ዓለሙ በ79ኛው ደቂቃ በራሷ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። የድሬዳዋ ከተማዋ መዓዛ አብደላ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጣለች። ከአምስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ድሬዳዋ ከተማ በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 10ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ ባለፉት 14 የሊጉ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ይርጋጨፌ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 4 ለ 2፣ ቦሌ ክፍለ ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 21ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከመጋቢት 28 እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም በቱርክዬ በሚከናወነው የዩኤፋ የወዳጅነት ዋንጫ ዝግጅት እና ተሳትፎ ያደርጋል። በብሔራዊ ቡድኑ ተሳትፎ ምክንያት የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ እንደሚቋረጥ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ቦሌ ክፍለ ከተማ ድል ቀንቶታል
Mar 26, 2026 68
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ቦሌ ክፍለ ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 ረቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ምህረት በቀለ ሁለቱንም ግቦች አስቆጥራለች። ምህረት አየለ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል የተመለሰው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ34 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ያሸነፋቸው ጨዋታዎች ብዛት ዘጠኝ ደርሰዋል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ባህር ዳር ከተማ በ16 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ለዩኤፋ ፍሬንድሺፕ ካፕ ውድድር ለ22 ተጫዋቾች ጥሪ ቀረበ
Mar 26, 2026 62
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በቱርክዬ ለሚከናወነው የዩኤፋ ፍሬንድሺፕ ዋንጫ ውድድር አሰልጣኝ ቻለው ለሜቻ ለ22 ተጫዋቾች ጥሪ አድርገዋል። ስመኝሽ ፍቃዱ (አዳማ ከተማ) እና ሊንጎ ኦማን (ቦሌ ክፍለ ከተማ) ጥሪ የተደረገላቸው ግብ ጠባቂዎች ናቸው። በተከላካይ መስመር አሶሬ ሃይሶ (ባህር ዳር ከተማ )፣ ፍቅርአዲስ ገዛኸኝ ( ቦሌ ክፍለ ከተማ) ፣ ለምለም አስታጥቄ (ሃዋሳ ከተማ )፣ ሳባ ኃይለሚካኤል (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ቤተልሄም መስፍን (ሃዋሳ ከተማ)፣ ከአምላክነሽ ሃንኮ (ሃዋሳ ከተማ)፣ ዝናሽ ሰለሞን (ድሬዳዋ ከተማ) እና ወርቅነሽ ዘሪሁን (ሸገር ከተማ) ጥሪ ተደርጎላቸዋል። ቱሪስት ቱንጋ (አዳማ ከተማ) ዙፋን ደፈርሻ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ሚለን ጋይም (ቦሌ ክፍለ ከተማ)፣ ሜላት ጌታቸው (ቦሌ ክፍለ ከተማ)፣ ብርሃን ኃይለስላሴ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ) እና ጋብሬላ አበበ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ) ቡድኑን እንዲቀላቀሉ ጥሪ ቀርቦላቸዋል። ታሪኳ ጴጥሮስ (ሃዋሳ ከተማ)፣ ምትኬ ብርሃኑ (ሲዳማ ቡና)፣ ቤዛዊት ንጉሴ (መቻል) ፣ ህዳት ካሱ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ሊዲያ ኢያሱ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ እና ማርያማዊት ታጠቅ (ኢትዮጵያ ስፖርት) በአጥቂ መስመር የሚገኙ ተጫዋቾች ናቸው። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ልምምዱን ከዛሬ ጀምሮ እንደሚያደርግ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር የሚያካሂደው የ’UEFA Frendship Cup’ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ውድድር በቱርክዬ አስተናጋጅነት ከመጋቢት 28 እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም ይከናወናል። በዚህ ውድድር ላይ ከተለያዩ አህጉራት የተውጣጡ ሀገራት የሚሳተፉ ሲሆን የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ጋር በፈጠረው ግንኙነት ከአፍሪካ ከሚሳተፉ ሁለት ሀገራት መካከል አንዱ መሆን ችሏል። በዚህም ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ይሳተፋል። በዚህ ውድድር ላይ አስተናጋጇ ቱርክዬን ጨምሮ ኢትዮጵያ፣ ኖርዌይ፣ ኡዝቤኪስታን፣ ኮስታሪካ፣ ፓራጓይ፣ ዩራጓይ እና ሞሮኮ ተሳታፊ እንደሚሆኑ የተረጋገጡ ቡድኖች ናቸው
ይርጋጨፌ ቡና ከ12 ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 26, 2026 54
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ይርጋጨፌ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 4 ለ 2 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ መንደሪን ክንድይሁን ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር አዳነች አስፋው እና ፍጹም ብርሃኑ ቀሪዎቹን ጎሎች ለይርጋጨፌ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አለሚ በዬቻ እና መሰረት ምክረ ለአዲስ አበባ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሁለት ግቦችን ያስቆጠረችው መንደሪን ክንድይሁን የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከ12 ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል የተመለሰው ይርጋጨፌ ቡና በ14 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 16ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዲስ አበባ ከተማ በ11 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዝግጅቱን ጀመረ
Mar 26, 2026 55
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ከደቡብ ሱዳን ጋር ለሚያደርጋቸው የመጀመርያ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች ዛሬ ልምምድ ማድረግ ጀምሯል። ማለዳ ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ልምምድ በአሰልጣኝ ራውዳ ዓሊ ጥሪ ከተደረገላቸው 23 ተጫዋቾች መካከል 16ቱ መገኘታቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ቀሪዎቹ ተጫዋቾች ከዛሬ የክለብ ጨዋታዎች በኃላ ተጠቃለው ወደ ስብስቡ እንደሚገቡም አመልክቷል። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ጨዋታዋን በሚያዚያ ወር 2018 ዓ.ም ከደቡብ ሱዳን ጋር ታደርጋለች።
ወደ ዓለም ዋንጫ የሚያልፉ ቀሪ ስድስት ሀገራት የሚለዩባቸው የማጣሪያ ጨዋታዎች
Mar 26, 2026 113
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በአሜሪካ፣ ሜክሲኮ እና ካናዳ ጣምራ አዘጋጅነት ከሰኔ 4 እስከ ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። በዓለም ዋንጫው 48 ሀገራት የሚሳተፉ ሲሆን፤ እስከ አሁን 42 ሀገራት የተሳትፎ ትኬታቸውን ቆርጠዋል። በውድድሩ ላይ የሚሳተፉ ቀሪ ስድስት ሀገራት የሚለዩባቸው የመጀመሪያ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ጥሎ ማለፍ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ይከናወናሉ። ምሽት 2 ሰዓት ላይ ቱርክዬ ከሮማንያ በቱፕራስ ስታዲየም ይጫወታሉ። የአራት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ጣልያን ከሰሜን አየርላንድ፣ ዴንማርክ ከሰሜን ሜቄዶኒያ፣ ፖላንድ ከአልባኒያ፣ ቼክ ሪፐብሊክ ከአየርላንድ፣ ዩክሬን ከስዊድን፣ ስሎቫኪያ ከኮሶቮ እና ዌልስ ከቦሲኒያ እና ሄርዞጌቪና በተመሳሳይ ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ45 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የዛሬውን ጨዋታ የሚያሸንፉ ሀገራት ለዓለም ዋንጫው ለማለፍ ወደሚደረገው የመጨረሻ ማጣሪያ ያልፋሉ። በመጨረሻው ማጣሪያ የጣልያን እና ሰሜን አየርላንድ አሸናፊ ከዌልስ እና ቦሲኒያና ሄርዜጎቪና አሸናፊ፣ የፖላንድ እና አልባኒያ አሸናፊ ከዩክሬንና ስዊድን አሸናፊ፣ የቱርክዬና ሮማኒያ አሸናፊ ከስሎቫኪያና ኮሶቮ አሸናፊ እንዲሁም የዴንማርክ እና ሰሜን ሜቄዶኒያ አሸናፊ ከቼክ ሪፐብሊክ እና አየርላንድ አሸናፊ ጋር ይጫወታሉ። የመጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጨዋታዎችን የሚያሸንፉ አራት ሀገራት ለዓለም ዋንጫ ማለፋቸውን ያረጋግጣሉ። አራቱ ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ከአውሮፓ 16 ሀገራት ይሳተፋሉ። በተያያዘም የክፍለ አህጉራት የዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ የመጀመሪያ ጨዋታዎችም ይካሄዳሉ። በማጣሪያው ላይ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ (አፍሪካ)፣ ኢራቅ (እስያ)፣ ቦሊቪያ (ደቡብ አሜሪካ)፣ ሱሪናም (ሰሜን/ማዕከላዊ አሜሪካ እና ካሪቢያን)፣ ጃማካይ (ሰሜን/ማዕከላዊ አሜሪካ እና ካሪቢያን) እና ኒው ካሌዶኒያ (ኦሽንያ) ይሳተፋሉ። በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ ያላቸው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ (48ኛ) እና ኢራቅ (55ኛ) በቀጥታ ወደ መጨረሻው የማጣሪያ ጨዋታ አልፈዋል። ቀሪዎቹ አራት ሀገራት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታቸውን በሜክሲኮ ያደርጋሉ። ቦሊቪያ ከሱሪናም ከሌሊቱ 7 ሰዓት በስታዲዩ ቢቢቪኤ፣ ኒው ካሌዶኒያ ከጃማይካ በአክሮን ስታዲየም ከጠዋቱ 12 ላይ ይጫወታሉ። የኒው ካሌዶኒያ እና ጃማይካ አሸናፊ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ የቦሊቪያ እና ሱሪናም አሸናፊ ከኢራቅ ጋር ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የመጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታቸውን ያሸነፉ ሁለት ሀገራት ለዓለም ዋንጫው ያልፋሉ።
የመውረድ ስጋት ያለባቸው ክለቦች የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Mar 26, 2026 90
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ይርጋጨፌ ቡና ከአዲስ አበባ ከተማ በአበባ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በ13ቱ ተሸንፎ በአምስቱ አቻ ወጥቷል። በ20ዎቹ ጨዋታዎች ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 31 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በ11 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ 20 ጨዋታዎች አከናውኖ ሶስት ጊዜ ድል ሲቀናው፤ በ15ቱ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 12 ግቦችን ሲያስቆጥር 41 ጎሎችን አስተናግዷል። አዲስ አበባ ከተማ በተመሳሳይ 11 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ 13ኛ ደረጃን በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ይርጋጨፌ ቡና ባለፉት 12 የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በአንጻሩ አዲስ አበባ ከተማ ካሸነፈ ከወራጅ ቀጠና ይወጣል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ድሬዳዋ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ድሬዳዋ ከተማ እስከ አሁን በሊጉ ማሸነፍ የቻለው ጨዋታ ብዛት ስድስት ነው። 11 ጊዜ ሲሸነፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 18 ግቦችን ሲያስቆጥር 31 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ21 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ 20 ጨዋታዎችን አድርጎ ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ፤ 14 ጊዜ ተሸንፏል። በአራት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 10 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 37 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት አምስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። አርባምንጭ ከተማ ባለፉት 13 ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ ላለመውረድ በሚደረገው ፉክክር ወሳኝ የሚባሉ ናቸው። ቦሌ ክፍለ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ31 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ባህር ዳር ከተማ በ16 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ቦሌ ክፍለ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ባህር ዳር ከተማ ካሸነፈ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Mar 25, 2026 81
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሲዳማ ቡናን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ህዳት ካሡ ግቦቹን አስቆጥራለች። ግቦቹን ያስቆጠረችው ህዳት ካሡ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከሁለት የአቻ ውጤቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ54 ነጥብ ከመሪው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር በነጥብ እኩል በመሆን በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በሊጉ 17ኛ ድሉንም አስመዝግቧል። የሁለቱ ቡድኖች በነጥብ እኩል መሆን የዋንጫ ፉክክሩን የበለጠ ሳቢ አድርጎታል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመቻል ጋር አንድ አቻ ተለያይቷል።
አዲስ አበባን ጽዱ፣ ውብና አረንጓዴ በማድረግ ለወጣቶች ምቹ የልማት ማዕከል የመገንባት ራዕይ በተግባር እየተረጋገጠ ነው
Mar 25, 2026 70
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ አዲስ አበባን ጽዱ፣ ውብና አረንጓዴ በማድረግ ለወጣቶች ምቹ የመዝናኛና የልማት ማዕከል የመገንባት ሥራ በተግባር እየተረጋገጠ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ በአራዳ ፓርክ የወጣቶች የኪነ-ጥበብ እና የፈጠራ ስራዎች የቀረቡበት መርሀ-ግብር አካሂዷል፡፡ የቢሮው ኃላፊ አቶ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ በዚሁ ወቅት፤ ከተማ አስተዳደሩ ወጣቶችን ታሳቢ ያደረጉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ማቀድ ብቻ ሳይሆን በተግባር በመፈጸም ውጤታማነቱን እያሳየ ይገኛል። በወንዝ ዳርቻና በኮሪደር ልማት የተገነቡ የወጣት ማዕከላት የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትልቅ ሚና በመጫወት ላይ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ በአራዳ ፓርክ የተካሄደው ወጣቶች የተሳተፉበት የባህላዊ ውዝዋዜ፣ የኪነ ጥበብ እና የፈጠራ ስራዎች መርሃ-ግብር ለዚህ ስኬት አብነት መሆኑን ጠቅሰዋል። እነዚህ ስፍራዎች ወጣቶች አብሮነታቸውንና ወንድማማችነታቸውን የሚያጠናክሩባቸው የጋራ መድረኮች ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉም ብለዋል። መሰል የማዘውተሪያ ስፍራዎች ወጣቶች በሀገራቸው ላይ ትልቅ ተስፋ እንዲሰንቁና የፈጠራ አቅማቸውን ወደ ላቀ ደረጃ እንዲያሸጋግሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱ አስረድተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች ማህበር ፕሬዝዳንት ምንያህል ጌታቸው እንዳለውም፣ አዲስ አበባ እንደ ስሟ እያበበች መሆኗን ገልጿል። የተገነቡት ማራኪ የመዝናኛ ስፍራዎች መንግስት ለወጣቱ ትውልድ የሚሰጠውን ልዩ ትኩረት የሚያሳዩና ተጠቃሚነትን በተጨባጭ ያረጋገጡ ስኬቶች መሆናቸውን ተናግሯል። ወጣት አርሴማ ሽመልስ በበኩሏ ቀደም ባሉት ጊዜያት በከተማዋ በቂ የወጣቶች መዝናኛ ስፍራዎች እንዳልነበሩ አስታውሳ አሁን የተገነቡት ስፍራዎች ለዓይን ማራኪ ከመሆናቸው ባለፈ፣ ወጣቶች ተሰጧቸውን የሚያሳዩበት ሰፊ ዕድል ፈጥሯል ብላለች፡፡
የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነጥብ ጣለ
Mar 25, 2026 79
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና መቻል አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ንግሥት በቀለ በ66ኛው ደቂቃ ባስቆጠረችው ጎል ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሪ ሆኗል። ጨዋታው በንግድ ባንክ አሸናፊነት ተጠናቀቀ ሲባል ቱሪስት ለማ በ91ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፈችው ግብ መቻል ወሳኝ አንድ ነጥብ አግኝቷል። ለመቻል ግቡን ያስቆጠረችው ቱሪስት ለማ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነጥቡን ወደ 54 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማስፋት እድል አልተጠቀመበትም። መቻል በ45 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ በሊጉ አምስተኛ ተከታታይ ድሉን የማስመዝገብ ሙከራው አልተሳካም።
የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታዎች
Mar 25, 2026 91
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሠዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመቻል በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በ17ቱ ድል ሲቀናው አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 58 ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ንግድ ባንክ በ53 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በሊጉ እስከ አሁን 20 ጨዋታዎች አከናውኖ 13 ጊዜ ሲያሸንፍ፤ በሁለቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 37 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያገናኝ 11 ግቦች ተቆጥረውበታል። መቻል በ44 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ መሪነቱን ያጠናክራል። መቻል ካሸነፈ በሊጉ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። በ20ኛ ሳምንት ከቦሌ ክፍለ ከተማ በተደረገው ጨዋታ በቀይ ካርድ የወጣችው የመቻል አጥቂ ሴናፍ ዋቁማ በዛሬው ጨዋታ አትሰለፍም። ሁለቱ ቡድኖች በጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። ቡድኖቹ በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት የሊጉ ጨዋታ ያለ ግብ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ20 የሊጉ ጨዋታዎች በ16ቱ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ20ዎቹ ጨዋታዎች ላይ 44 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 11 ግቦች ተቆጥረውበታል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ51 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በውድድር ዓመቱ 20 ጨዋታዎች አድርጎ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ፤ በተመሳሳይ በስምንት ጨዋታዎች ሽንፈት አጋጥሞታል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 20 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 25 ጎሎችን አስተናግዷል። ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ ማግኘት ለቡድኑ የዋንጫ ፉክክር ወሳኝ ነው። በ20ኛ ሳምንት ከድሬዳዋ ከተማ ጋር አንድ አቻ የተለያየው ሲዳማ ቡና ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። የዛሬ ጨዋታዎች በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ የሚባሉ ናቸው።
መሐመድ ሳላህ ሊቨርፑልን በዓመቱ መጨረሻ ይለቃል
Mar 25, 2026 139
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፦ የሊቨርፑሉ ኮከብ መሐመድ ሳላህ በውድድር ዓመቱ መጨረሻ ክለቡን እንደሚለቅ በይፋ አስታወቀ። ሳላህ ይህን ውሳኔውን ያሳወቀው ለደጋፊዎቹ ባስተላለፈው የቪዲዮ መልዕክት ነው። "ይህ ቀን በመምጣቱ አዝናለሁ... በውድድር ዓመቱ መጨረሻ ሊቨርፑልን እለቃለሁ። ይህ ክለብ፣ ይህች ከተማ እና ደጋፊዎቹ በህይወቴ ውስጥ ምን ያህል ትልቅ ቦታ እንዳላችሁ መግለጽ ይከብደኛል" ብሏል። የሊቨርፑል ክለብ ባወጣው መግለጫ ሳላህ የዘጠኝ ዓመት የክለብ ቆይታውን በሰኔ 2026 (እ.ኤ.አ) እንደሚያበቃ አስታውቋል። ተጫዋቹ ለደጋፊዎቹ ግልጽነት ለመፍጠር ሲል ውሳኔውን አሁን ለማሳወቅ መምረጡን ቢቢሲ ዘግቧል። ባለፉት ወራት በሳላህ እና በአሰልጣኝ አርኔ ስሎት መካከል የነበረው ግንኙነት መሻከር እና የተጫዋቹ የመሰለፍ ዕድል መቀነስ ለዚህ ውሳኔ በምክንያትነት ይጠቀሳሉ። ክለቡ እና ተጫዋቹ በጋራ ስምምነት ለመለያየት ወስነዋል። ሳላህ ምንም እንኳን የቀጣይ ክለቡ በይፋ ባይታወቅም፤ የሳዑዲ ዓረቢያ ክለቦች (በተለይም አል-ኢትሀድ) ተጫዋቹን ለመውሰድ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸውና ድርድር ላይ እንደሆኑ በስፋት እየተዘገበ ይገኛል። የ33 ዓመቱ ሳላህ በሊቨርፑል 435 ጨዋታዎችን አድርጎ 255 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ይህም ከኢያን ራሽ (346 ጎሎች) እና ከሮጀር ሀንት (285 ጎሎች) በመቀጠል በሊቨርፑል የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ዝርዝር ውስጥ በሶስተኝነት ደረጃ ላይ እንዲቀመጥ አድርጎታል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር በሚያዝያ ወር ይካሄዳል
Mar 24, 2026 231
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ከሚያዝያ 14 እስከ 17 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄዱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታወቀ። በዚሁ መሰረት ቦዲቲ ከተማ ከመቀሌ 70 እንደርታ፣ ቤንች ማጂ ቡና ከኢትዮጵያ መድን፣ መቻል ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ነገሌ አርሲ ከሲዳማ ቡና ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ በአዲስ አበባ ስታዲየም እንደሚደረጉ ፌዴሬሽኑ ገልጿል።
ሃዋሳ ከተማ እና ሸገር ከተማ ነጥብ ተጋሩ
Mar 24, 2026 100
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሃዋሳ ከተማ እና ሸገር ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው የተካሄደው በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ነው። የሸገር ከተማዋ ወርቅነሽ ዘሪሁን የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ሃዋሳ ከተማ በ43 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ሸገር ከተማ በ40 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ የ21ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ልደታ ክፍለ ከተማ አዳማ ከተማን 4 ለ 1 አሸንፏል።
ልደታ ክፍለ ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 24, 2026 82
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ልደታ ክፍለ ከተማ አዳማ ከተማን 4 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሰርካለም ሻፊ ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር ይታገሱ ተገኘወርቅ እና እመቤት ፋንታሁን ቀሪዎቹን ጎሎች ለልደታ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሳሮን ካሳ ለአዳማ ከተማ ብቸኛውን ጎል አስቆጥራለች። የልደታ ክፍለ ከተማዋ ይታገሱ ተገኘወርቅ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጣለች። ከአራት የሊጉ ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ልደታ ክፍለ ከተማ በ18 ነጥብ ደረጃውን ከ11ኛ ወደ 10ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ ያስመዘገባቸውን ድሎች ብዛት አምስት አድርሷል። በአንጻሩ በሊጉ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም።
የብሔራዊ ቡድኑ አምበል ጋቶች ፓኖም ወደ ሞሮኮ አያመራም
Mar 24, 2026 97
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አምበል ጋቶች ፓኖም በወላጅ አባቱ ድንገተኛ ህልፈት ምክንያት ወደ ሞሮኮ ከሚጓዘው ልዑክ ሳይካተት መቅረቱን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታወቀ። እግር ኳስ ፌዴሬሽንእና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አባላት በጋቶች ፓኖም ወላጅ አባት ህልፈት የተሰማቸውን ጥልቅ ሀዘን በመግለጽ ለተጫዋቹ እና ለቤተሰቡ መጽናናትን ተመኝተዋል። ብሔራዊ ቡድኑ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንስፔ ጋር ለሚያደርገው የ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታ ዛሬ ረፋድ ላይ ወደ ሞሮኮ ያቀናል።
ሃዋሳ ከተማ ከሸገር ከተማ ጋር ይጫወታል
Mar 24, 2026 82
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። ከቀኑ 9 ሰዓት ሃዋሳ ከተማ ከሸገር ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ 20 ጨዋታዎች አድርጎ 12 ጊዜ ድል ሲቀናው በሁለቱ ተሸንፏል። በስድስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 34 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 12 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ42 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 20 ጨዋታዎች መካከል 12ቱን ያሸነፈው ሸገር ከተማ በበኩሉ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። በ20 ጨዋታዎች 33 ግቦችን ሲያስቆጥር 23 ጎሎችን አስተናግዷል። ሸገር ከተማ በ39 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሃዋሳ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ካሸነፈ ከመቻል የሶስተኝነት ደረጃን በጊዜያዊነት ይረከባል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ሸገር ከተማ ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ልደታ ክፍለ ከተማ ከአዳማ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአበበ በቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ልደታ ክፍለ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በአራቱ አሸንፎ በ13ቱ ተሸንፎ በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 21 ግቦችን ሲያስቆጥር 40 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ15 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው አዳማ ከተማ እስከ አሁን በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 20 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ሲያሸንፍ በዘጠኙ ሽንፈት አስተናግዷል። ስድስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 14 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 37 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ልደታ ክፍለ ከተማ ባለፉት አራት ጨዋታዎች፣ አዳማ ከተማ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፉም። ሁለቱም ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት እስከ መጋቢት 17 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሊጉን በ53 ነጥብ ይመራል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ51 ነጥብ ይከተላል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን በ22 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራች ነው። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ በ16 ጎሎች ትከተላለች።
55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ ይጀመራል
Mar 24, 2026 138
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ):- 55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በአደይ አበባ ዓለም አቀፍ ስቴዲየም ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል። ሻምፒዮናው ተተኪ አትሌቶችን ለማፍራት፣ ለአትሌቶች የውድድር እድል ለመፍጠር ፣ አትሌቶችን በሽልማት ለማበረታታት ዓላማ ያደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በውድድሩ ላይ 36 ክለቦችና ተቋማት እና 9 ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የሚሳተፉ ሲሆን 621 ወንድ፣ 436 ሴት በድምሩ 1057 ተወዳዳሪዎች እንደሚሳተፉ አመልክቷል። ፌዴሬሽኑ ለውድድሩ ማስኬጃ ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ እንደመደበ አመልክቷል። በሻምፒዮናው መክፈቻ የተለያዩ ውድድሮች ይካሄዳሉ። በውድድሩ ላይ ዘመናዊ የሰዓት መቆጣጠሪያ ቴክኖሎጂ (Time Tronics) ተግባራዊ እንደሚሆንም ተመላክቷል። 55ኛው የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ሻምፒዮና እስከ መጋቢት 20 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
በሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ለ23 ተጫዋቾች ጥሪ ተደረገ
Mar 23, 2026 180
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ከደቡብ ሱዳን ጋር ለሚያደርጋቸው የመጀመርያ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች አሰልጣኝ ራውዳ ዓሊ ለ23 ተጫዋቾች ጥሪ አቅርበዋል። ግብ ጠባቂዎች መቲ ረታ (ልደታ )፣ ኑዳ ሁሴን (አዲስ ከተማ ) እና ኢትዮጵያ ለማ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ) ጥሪ ተደርጎላቸዋል። ማንጠግቦሽ አድማሱ (አርባምንጭ ከተማ )፣ ኤልሻዳይ ዮሴፍ ( ጉለሌ) ፣ ሴና ኤርሚያስ (ለሚኩራ )፣ ቤተልሄም ጌታቸው (ንፋስ ስልክ ላፍቶ)፣ መድሃኒት አለሙ (አርባምንጭ ከተማ) እና መሰረት ጌታቸው (ኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ) በተከላካይ መስመር የሚገኙ ተጫዋቾች ናቸው። በአማካይ ክፍል ኑአሚን ከበደ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ ኢክራም ሚፍታህ (ደራርቱ ቱሉ አካዳሚ )፣ ትዕግስት ተሾመ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ ሊያም ዳንኤል (ኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ)፣ ቢታኒያ አስተረፍ (ሲዳማ ቡና) ፣ ሊዲያ ሰለሞን (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ) እና ምህረት ወሰኑ (ሸገር ከተማ) በጥሪው ተካትተዋል። ሲርይ ተሾመ (ጉለሌ)፣ ኦጁሉ ኦዶንግ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ ምህረት አየለ (ቦሌ ክፍለ ከተማ) ፣ ማህሌት ደመቀ (ሐምሌ 19 ክለብ)፣ እመቤት ዘካሪያስ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ ሙሉ አበራ (ለሚ ኩራ) እና ሰሊና ናግዋ (ጉለሌ) በአጥቂ መስመር ጥሪ ቀርቦላቸዋል። ጥሪ የተደረገላቸው ተጫዋቾች መጋቢት 16 ቀን 2018 ዓ.ም ዝግጅታቸውን እንደሚጀምሩ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ጨዋታዋን በሚያዚያ ወር 2018 ዓ.ም ታደርጋለች።