ቀጥታ፡
ስፖርት
አዲስ አበባን ጽዱ፣ ውብና አረንጓዴ በማድረግ ለወጣቶች ምቹ የልማት ማዕከል የመገንባት ራዕይ በተግባር እየተረጋገጠ ነው
Mar 25, 2026 49
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ አዲስ አበባን ጽዱ፣ ውብና አረንጓዴ በማድረግ ለወጣቶች ምቹ የመዝናኛና የልማት ማዕከል የመገንባት ሥራ በተግባር እየተረጋገጠ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ በአራዳ ፓርክ የወጣቶች የኪነ-ጥበብ እና የፈጠራ ስራዎች የቀረቡበት መርሀ-ግብር አካሂዷል፡፡   የቢሮው ኃላፊ አቶ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ በዚሁ ወቅት፤ ከተማ አስተዳደሩ ወጣቶችን ታሳቢ ያደረጉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ማቀድ ብቻ ሳይሆን በተግባር በመፈጸም ውጤታማነቱን እያሳየ ይገኛል። በወንዝ ዳርቻና በኮሪደር ልማት የተገነቡ የወጣት ማዕከላት የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትልቅ ሚና በመጫወት ላይ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ በአራዳ ፓርክ የተካሄደው ወጣቶች የተሳተፉበት የባህላዊ ውዝዋዜ፣ የኪነ ጥበብ እና የፈጠራ ስራዎች መርሃ-ግብር ለዚህ ስኬት አብነት መሆኑን ጠቅሰዋል። እነዚህ ስፍራዎች ወጣቶች አብሮነታቸውንና ወንድማማችነታቸውን የሚያጠናክሩባቸው የጋራ መድረኮች ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉም ብለዋል። መሰል የማዘውተሪያ ስፍራዎች ወጣቶች በሀገራቸው ላይ ትልቅ ተስፋ እንዲሰንቁና የፈጠራ አቅማቸውን ወደ ላቀ ደረጃ እንዲያሸጋግሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱ አስረድተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች ማህበር ፕሬዝዳንት ምንያህል ጌታቸው እንዳለውም፣ አዲስ አበባ እንደ ስሟ እያበበች መሆኗን ገልጿል። የተገነቡት ማራኪ የመዝናኛ ስፍራዎች መንግስት ለወጣቱ ትውልድ የሚሰጠውን ልዩ ትኩረት የሚያሳዩና ተጠቃሚነትን በተጨባጭ ያረጋገጡ ስኬቶች መሆናቸውን ተናግሯል።   ወጣት አርሴማ ሽመልስ በበኩሏ ቀደም ባሉት ጊዜያት በከተማዋ በቂ የወጣቶች መዝናኛ ስፍራዎች እንዳልነበሩ አስታውሳ አሁን የተገነቡት ስፍራዎች ለዓይን ማራኪ ከመሆናቸው ባለፈ፣ ወጣቶች ተሰጧቸውን የሚያሳዩበት ሰፊ ዕድል ፈጥሯል ብላለች፡፡      
የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታዎች 
Mar 25, 2026 75
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ።   ከረፋዱ አራት ሠዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመቻል በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በ17ቱ ድል ሲቀናው አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 58 ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ንግድ ባንክ በ53 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በሊጉ እስከ አሁን 20 ጨዋታዎች አከናውኖ 13 ጊዜ ሲያሸንፍ፤ በሁለቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 37 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያገናኝ 11 ግቦች ተቆጥረውበታል። መቻል በ44 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ መሪነቱን ያጠናክራል። መቻል ካሸነፈ በሊጉ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። በ20ኛ ሳምንት ከቦሌ ክፍለ ከተማ በተደረገው ጨዋታ በቀይ ካርድ የወጣችው የመቻል አጥቂ ሴናፍ ዋቁማ በዛሬው ጨዋታ አትሰለፍም። ሁለቱ ቡድኖች በጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። ቡድኖቹ በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት የሊጉ ጨዋታ ያለ ግብ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው።   በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ20 የሊጉ ጨዋታዎች በ16ቱ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ20ዎቹ ጨዋታዎች ላይ 44 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 11 ግቦች ተቆጥረውበታል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ51 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በውድድር ዓመቱ 20 ጨዋታዎች አድርጎ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ፤ በተመሳሳይ በስምንት ጨዋታዎች ሽንፈት አጋጥሞታል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 20 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 25 ጎሎችን አስተናግዷል። ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ ማግኘት ለቡድኑ የዋንጫ ፉክክር ወሳኝ ነው። በ20ኛ ሳምንት ከድሬዳዋ ከተማ ጋር አንድ አቻ የተለያየው ሲዳማ ቡና ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። የዛሬ ጨዋታዎች በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ የሚባሉ ናቸው።
መሐመድ ሳላህ ሊቨርፑልን በዓመቱ መጨረሻ ይለቃል
Mar 25, 2026 123
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፦ የሊቨርፑሉ ኮከብ መሐመድ ሳላህ በውድድር ዓመቱ መጨረሻ ክለቡን እንደሚለቅ በይፋ አስታወቀ። ሳላህ ይህን ውሳኔውን ያሳወቀው ለደጋፊዎቹ ባስተላለፈው የቪዲዮ መልዕክት ነው።   "ይህ ቀን በመምጣቱ አዝናለሁ... በውድድር ዓመቱ መጨረሻ ሊቨርፑልን እለቃለሁ። ይህ ክለብ፣ ይህች ከተማ እና ደጋፊዎቹ በህይወቴ ውስጥ ምን ያህል ትልቅ ቦታ እንዳላችሁ መግለጽ ይከብደኛል" ብሏል። የሊቨርፑል ክለብ ባወጣው መግለጫ ሳላህ የዘጠኝ ዓመት የክለብ ቆይታውን በሰኔ 2026 (እ.ኤ.አ) እንደሚያበቃ አስታውቋል።   ተጫዋቹ ለደጋፊዎቹ ግልጽነት ለመፍጠር ሲል ውሳኔውን አሁን ለማሳወቅ መምረጡን ቢቢሲ ዘግቧል። ባለፉት ወራት በሳላህ እና በአሰልጣኝ አርኔ ስሎት መካከል የነበረው ግንኙነት መሻከር እና የተጫዋቹ የመሰለፍ ዕድል መቀነስ ለዚህ ውሳኔ በምክንያትነት ይጠቀሳሉ። ክለቡ እና ተጫዋቹ በጋራ ስምምነት ለመለያየት ወስነዋል። ሳላህ ምንም እንኳን የቀጣይ ክለቡ በይፋ ባይታወቅም፤ የሳዑዲ ዓረቢያ ክለቦች (በተለይም አል-ኢትሀድ) ተጫዋቹን ለመውሰድ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸውና ድርድር ላይ እንደሆኑ በስፋት እየተዘገበ ይገኛል።   የ33 ዓመቱ ሳላህ በሊቨርፑል 435 ጨዋታዎችን አድርጎ 255 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ይህም ከኢያን ራሽ (346 ጎሎች) እና ከሮጀር ሀንት (285 ጎሎች) በመቀጠል በሊቨርፑል የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ዝርዝር ውስጥ በሶስተኝነት ደረጃ ላይ እንዲቀመጥ አድርጎታል።
ሃዋሳ ከተማ ከሸገር ከተማ ጋር ይጫወታል 
Mar 24, 2026 79
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል። ከቀኑ 9 ሰዓት ሃዋሳ ከተማ ከሸገር ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ሃዋሳ ከተማ በሊጉ 20 ጨዋታዎች አድርጎ 12 ጊዜ ድል ሲቀናው በሁለቱ ተሸንፏል። በስድስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። 34 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 12 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ42 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 20 ጨዋታዎች መካከል 12ቱን ያሸነፈው ሸገር ከተማ በበኩሉ በአምስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። በ20 ጨዋታዎች 33 ግቦችን ሲያስቆጥር 23 ጎሎችን አስተናግዷል። ሸገር ከተማ በ39 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።   ሃዋሳ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ካሸነፈ ከመቻል የሶስተኝነት ደረጃን በጊዜያዊነት ይረከባል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ሸገር ከተማ ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ልደታ ክፍለ ከተማ ከአዳማ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአበበ በቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ልደታ ክፍለ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በአራቱ አሸንፎ በ13ቱ ተሸንፎ በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 21 ግቦችን ሲያስቆጥር 40 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ15 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።   ተጋጣሚው አዳማ ከተማ እስከ አሁን በውድድር ዓመቱ ካከናወናቸው 20 ጨዋታዎች መካከል አምስቱን ሲያሸንፍ በዘጠኙ ሽንፈት አስተናግዷል። ስድስት ጊዜ ነጥብ ተጋርቷል። 14 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 37 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ልደታ ክፍለ ከተማ ባለፉት አራት ጨዋታዎች፣ አዳማ ከተማ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፉም። ሁለቱም ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት እስከ መጋቢት 17 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሊጉን በ53 ነጥብ ይመራል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ51 ነጥብ ይከተላል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰለሞን በ22 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራች ነው። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ በ16 ጎሎች ትከተላለች።
በሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ለ23 ተጫዋቾች ጥሪ ተደረገ
Mar 23, 2026 175
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ከደቡብ ሱዳን ጋር ለሚያደርጋቸው የመጀመርያ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች አሰልጣኝ ራውዳ ዓሊ ለ23 ተጫዋቾች ጥሪ አቅርበዋል። ግብ ጠባቂዎች መቲ ረታ (ልደታ )፣ ኑዳ ሁሴን (አዲስ ከተማ ) እና ኢትዮጵያ ለማ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ) ጥሪ ተደርጎላቸዋል። ማንጠግቦሽ አድማሱ (አርባምንጭ ከተማ )፣ ኤልሻዳይ ዮሴፍ ( ጉለሌ) ፣ ሴና ኤርሚያስ (ለሚኩራ )፣ ቤተልሄም ጌታቸው (ንፋስ ስልክ ላፍቶ)፣ መድሃኒት አለሙ (አርባምንጭ ከተማ) እና መሰረት ጌታቸው (ኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ) በተከላካይ መስመር የሚገኙ ተጫዋቾች ናቸው። በአማካይ ክፍል ኑአሚን ከበደ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ ኢክራም ሚፍታህ (ደራርቱ ቱሉ አካዳሚ )፣ ትዕግስት ተሾመ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ ሊያም ዳንኤል (ኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ)፣ ቢታኒያ አስተረፍ (ሲዳማ ቡና) ፣ ሊዲያ ሰለሞን (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ) እና ምህረት ወሰኑ (ሸገር ከተማ) በጥሪው ተካትተዋል። ሲርይ ተሾመ (ጉለሌ)፣ ኦጁሉ ኦዶንግ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ ምህረት አየለ (ቦሌ ክፍለ ከተማ) ፣ ማህሌት ደመቀ (ሐምሌ 19 ክለብ)፣ እመቤት ዘካሪያስ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ ሙሉ አበራ (ለሚ ኩራ) እና ሰሊና ናግዋ (ጉለሌ) በአጥቂ መስመር ጥሪ ቀርቦላቸዋል። ጥሪ የተደረገላቸው ተጫዋቾች መጋቢት 16 ቀን 2018 ዓ.ም ዝግጅታቸውን እንደሚጀምሩ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ጨዋታዋን በሚያዚያ ወር 2018 ዓ.ም ታደርጋለች።
የሀላባ ቁሊቶ ስታዲዮም ግንባታ የአካባቢውን የስፖርት እንቅስቃሴ እያነቃቃ ነው
Mar 23, 2026 88
ሀላባ ቁሊቶ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ) :- የሀላባ ቁሊቶ ስታዲዮም ግንባታ የአካባቢውን የስፖርት እንቅስቃሴ እያነቃቃ መሆኑ ተገለጸ፡፡ በእግር ኳሱ ኢትዮጵያን የሚወክሉ ስፖርተኞች መፍለቂያ በሆነው የሃላባ ዞን የስፖርት መሰረተ ልማት አለመኖር በርካታ ብቁ ስፖርተኞችን ለማፍራት ተግዳሮት ሆኖ ቆይቷል። አሁን ላይ ለዘርፉ በተሰጠው ትኩረት ደረጃውን የጠበቀ ስታዲዮም ግንባታ መጀመሩ ለአካባቢው የስፖርት እንቅስቃሴ መነቃቃት መፍጠሩን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ነዋሪዎች ተናግረዋል።   ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ንጋቱ መለሰ እና አቶ ሳባቶ አህመድ እንደገለጹት ሀላባ ዞን በእግር ኳስ ስፖርት ትልቅ ስም የነበረው ቢሆንም በትኩረት ማነስና በመሰረተ ልማት እጦት ማደግ በሚገባውና ባለው አቅም ልክ ማደግ አልቻለም።   በግንባታ ሂደት አገልግሎት መስጠት የጀመረው የሀላባ ቁሊቶ ስታዲዮም በዘርፉ የተፈጠረውን መቀዛቀዝ በመቀየር አካባቢውን የስፖርት ልማት ዘርፍ በከፍተኛ ሁኔታ ማነቃቃቱን ተናግረዋል። የስታዲዮሙ ግንባታ የእግር ኳስ አፍቃሪውን ዳግም ወደ ሜዳ የሚመልስና ሀገርን የሚወክሉ ስፖርተኞች እንዲፈልቁ የሚያደርግ ነው ብለዋል፡፡   የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ምድብ “ለ” ቡድኖች ጨዋታቸውን በስታዲዮሙ እያደረጉ ሲሆን አስተያየታቸውን የሰጡት የኤልቴክ እግር ኳስ ቡድን አሰልጣኝ ይገረም ኤሊያስ በጥሩ ሜዳ መጫወት ውጤትን ይወስናል ብለዋል።   ለስፖርት መሰረተ ልማት በተሰጠው ትኩረት ደረጃቸውን የጠበቁ ስታዲዮሞች መገንባት ለሀገሪቱ የእግር ኳስ ስፖርት ዕድገት ሚናው የጎላ መሆኑን ጠቁመዋል። የሃላባ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ታገል ጌታቸው በበኩላቸው፤ በህዝብ ተሳትፎ ግንባታው የተጀመረው የሀላባ ስታዲዮም የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን ገልጸዋል፡፡   ሰው ሰራሽ የመጫወቻ ሜዳ፣ የተመልካች መቀመጫ፣ የፍሳሽ ማስወገጃና ሌሎችም በመጀመሪያው ምእራፍ ግንባታ መጠናቀቃቸውን የገለጹት ሃላፊው በስፖርት ዘርፉ ከፍተኛ መነቃቃት ተፈጥሯል ብለዋል፡፡ የግንባታው ሁለተኛ ምዕራፍ አካል የሆኑት የመብራትና ዓለም አቀፍ መመዘኛ ያሟላ የክቡር ትሪቡን ግንባታ እየተካሄደ መሆኑን ጠቅሰዋል። አካባቢው በእግር ኳስ ክህሎት የዳበረና የላቀ ብቃት ያላቸው ተተኪ ስፖርተኞች የሚፈሩበት እንደሆነ ጠቅሰው ሜዳው አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ብቁ ስፖርተኞችን ለማፍራት እየተደረገ ያለውን ጥረት እንደሚደግፍም አመልክተዋል። ግንባታው በሁለት ምዕራፍ እየተከናወነ የሚገኘው ስታዲዮሙ የካፍ ስታንዳርድን ባሟላ መልኩ እየተገነባ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን ሲጠናቀቅም ክልላዊም፣ ሀገር አቀፍና ሌሎች ውድድሮችን ለማስተናገድ እንደሚያስችልም ተናግረዋል።
አሜሪካ በዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና አንደኛ ደረጃን ይዛ አጠናቀቀች
Mar 23, 2026 167
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦ አሜሪካ በ21ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና 18 ሜዳሊያዎችን በማግኘት አሸናፊ ሆናለች። በፖላንድ ቶሩን ከተማ ከመጋቢት 11 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ሲካሄድ የቆየው ሻምፒዮና ትናንት ማምሻውን ተጠናቋል። በሻምፒዮናው ከ118 ሀገራት የተወጣጡ 674 አትሌቶች ተሳትፈዋል። አሜሪካ በአምስት ወርቅ፣ በሰባት ብር እና ስድስት ነሐስ በአጠቃላይ 18 ሜዳሊያዎችን በማግኘት ውድድሩን በአንደኝነት አጠናቃለች። ታላቋ ብሪታኒያ (ሰሜን አየርላንድን ጨምሮ) በአራት ወርቅ ሁለተኛ ሆና ጨርሳለች። ጣልያን በሶስት የወርቅ እና ሁለት የብር በድምሩ አምስት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። ዩክሬን እና ፖርቹጋል በተመሳሳይ ሁለት የወርቅ እና አንድ ብር በድምሩ ሶስት ሜዳሊያዎችን አግኝተው አራተኛ ወጥተዋል። በውድድሩ ላይ ከተሳተፉ አፍሪካ ሀገራት የወርቅ ሜዳሊያ ያገኘ ሀገር የለም። ሴኔጋል እና አልጄሪያ በተመሳሳይ አንድ አንድ የነሐስ ሜዳሊያ በማግኘት 24ኛ ደረጃን ይዘው ውድድራቸውን አጠናቀዋል።   በሻምፒዮናው ላይ ከተሳተፉ 118 ሀገራት መካከል ሜዳሊያ ያገኙት 32ቱ ብቻ ናቸው። በሻምፒዮናው በስድስት አትሌቶች የተወከለችው ኢትዮጵያ ምንም ሜዳሊያ ሳታገኝ አጠናቃለች።
በደርቢው ጨዋታ ሪያል ማድሪድ አትሌቲኮ ማድሪድን አሸነፈ
Mar 23, 2026 116
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በስፔን ላሊጋ 29ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር ሪያል ማድሪድ አትሌቲኮ ማድሪድን 3 ለ 2 አሸንፏል። በበርናባው ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቪኒቨስ ጁኒየር በጨዋታ እና በፍጹም ቅጣት ምት ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ፌዴሪኮ ቫልቬርዴ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። አዴሞላ ሉክማን እና ናህኤል ሞሊና ለአትሌቲኮ ማድሪድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ግብ ያስቆጠረው የሪያል ማድሪዱ ቬዴሪኮ ቫልቬርዴ በ77ኛው ደቂቃ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥቷል። ቫልቬርዴ በወጣበት መንገድ የሪያል ማድሪድ ተጫዋቾች እና የአሰልጣኝ ቡድን አባላት ተቃውሟቸውን አሰምተዋል። ተቃውሞው ከቢጫ ካርድ ያለፈ አያሰጥም የሚል ነው።   ጨዋታው አዝናኝ እና ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። አትሌቲኮ ማድሪድ ያገኘውን የቁጥር ብልጫ ወስዶ ተጭኖ ቢጫወትም ግብ ማስቆጠር አልቻለም። 242ኛው የማድሪድ ደርቢ በሪያል ማድሪድ አሸናፊነት ተጠናቋል። ሁለት ግቦችን ያስቆጠረው ቪኒሸስ ጁኒየር የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። በሊጉ 22ኛ ድሉን ያስመዘገበው ሪያል ማድሪድ በ69 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ ባርሴሎና ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አራት ዝቅ አድርጓል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ነጥብ አግኝቷል። በውድድር ዓመቱ ስድስተኛ ሽንፈቱን አትሌቲኮ ማድሪድ በ57 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የሪያል ማድሪዱ አሰልጣኝ አልቫሮ አርቤሎአ በመጀመሪያ የማድሪድ ደርቢ ድል ቀንቶታል። በተያያዘም ዛሬ በተደረገ ሌላኛው ጨዋታ ባርሴሎና ራዮ ቫዮካኖን 1 ለ 0 በማሸነፍ በ73 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል።
ኢትዮጵያ በዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮናው ምንም ሜዳሊያ ሳታገኝ አጠናቀቀች
Mar 22, 2026 157
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በ21ኛው የዓለም አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ማምሻውን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የተሳተፉባቸው የፍጻሜ ውድድሮች ተደርገዋል። በ800 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ አትሌት ንግስት ጌታቸው 1 ደቂቃ ከ59 ሴኮንድ ከ73 ማይክሮ ሴኮንድ አራተኛ ወጥታለች። የታላቁ ብሪታኒያ አትሌት ኬሊ ሆድግኪንሰን 1 ደቂቃ ከ55 ሴኮንድ ከ 30 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። በርቀቱ የዓመቱን ፈጣን ሰዓት አስመዝግባለች። ስዊዘርላንዳዊቷ አውድሬይ ዌሮ ሁለተኛ እና አሜሪካዊቷ አዲሰን ዋይሊ ሶስተኛ ደረጃን ይዘው ውድድራቸውን አጠናቀዋል። በሴቶችም የ1500 ሜትር የፍጻሜ ውድድር አትሌት ብርቄ ኃየሎም 4 ደቂቃ ከ01 ሴኮንድ ከ34 ማይክሮ ሴኮንድ አምስተኛ ወጥታለች። የታላቋ ብሪታኒያ አትሌት ጆርጂያ ሀንተር ቤል 3 ደቂቃ ከ58 ሴኮንድ ከ53 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ በመውጣት የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። አውስትራሊያዊቷ ጄሲካ ሁል ሁለተኛ ስትወጣ አሜሪካዊቷ ኒኪ ሂልትዝ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቃለች። በሻምፒዮናው በስድስት አትሌቶች የተወከለችው ኢትዮጵያ ምንም ሜዳሊያ ሳታገኝ አጠናቃለች።
ማንችስተር ሲቲ ለዘጠነኛ ጊዜ የካራባኦ ዋንጫን አነሳ
Mar 22, 2026 221
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ካራባኦ ካፕ ፍጻሜ ማንችስተር ሲቲ አርሰናልን 2 ለ 0 አሸንፏል።   ማምሻውን በዌምብሌይ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኒኮ ኦራይሊ በ60ኛው እና በ64ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል።   ማንችስተር ሲቲ በሁለተኛው አጋማሽ ያሳየው የተሻለ እንቅስቃሴ ጨዋታውን እንዲያሸንፍ አድርጓታል።   አርሰናል በጨዋታው ግልጽ የግብ እድሎችን በበቂ ሁኔታ መፍጠር አልቻለም። የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የአርሰናል ደጋፊ የሆኑት ሰር ኪር ስታርመር ጨዋታውን በስታዲየም በመገኘት ተከታትለዋል።   ውጤቱን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ ለዘጠነኛ ጊዜ የካራባኦ ዋንጫን አንስቷል። ሲቲ ከሊቨርፑል (10 ዋንጫ) ቀጥሎ የውድድሩ ስኬታማ ክለብ ነው። ለአራት ዋንጫ የሚፎካከረው አርሰናል የመጀመሪያውን ዋንጫ አጥቷል።   ከ33 ዓመታት በኋላ የካራባኦ ዋንጫን የማሸነፍ ህልሙ አልተሳካም። መድፈኞቹ ከዚህ ቀደም ውድድሩን ለሁለት ጊዜ አሸንፈዋል። አርሰናል እና ማንችስተር ሲቲ በሊጉ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛሉ።
አስቶንቪላ ወሳኝ ድል አሳክቷል
Mar 22, 2026 117
አዲስ አበባ ፤ መጋቢት 13/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 31ኛ ሳምንት አስቶንቪላ ዌስትሃም ዩናይትድን 2 ለ 0 አሸንፏል። በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጆን ሚጊን እና ኦሊ ዋትኪንስ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አስቶንቪላ በ54 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ሶስተኛ ደረጃ ላይ ከሚገኘው ማንችስተር ዩናይትድ ጋር የነጥብ ልዩነት ወደ አንድ ዝቅ አድርጓል። በሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ፉክክር ወሳኝ ሶሶት ነጥብ አግኝቷል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ29 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኖቲንግሃም ፎረስት ቶተንሃም ሆትስፐርስን 3 ለ 0 አሸንፏል። በቶተንሃም ሆትስፐርስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኢጎር ጄሱስ፣ ሞርጋን ጊብስ ዋይት እና ታይዎ አዎኒ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኖቲንግሃም ፎረስት በ32 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በ30 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የሰሜን ለንደኑ ቡድን የመውረድ ስጋቱ እየጨመረ ይገኛል። በቲን ሳይድ ደርቢ ሰንደርላንድ ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ኬምስዳይን ታሊቢ እና ብሪያን ብሮቤይ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አንቶኒ ጎርደን ለኒውካስትል ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሰንደርላንድ በ43 ነጥብ 11ኛ፣ ኒውካስትል ዩናይትድ በ42 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዘዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም