ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 35ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል
May 1, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ35ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛሬ በሊድስ ዩናይትድ እና በርንሌይ መካከል ይካሄዳል። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ላይ በኢላንድ ሮድ ፓርክ ስታዲየም ይደረጋል። ሊድስ ዩናይትድ በ40 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መውረዱ የተረጋገጠው በርንሌይ በ20 ነጥብ 19ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በፕሪሚየር ሊጉ መድረክ ለስምንተኛ ጊዜ የሚገናኙ ሲሆን፣ በታሪክ ሊድስ ዩናይትድ የበላይነቱን ይዟል። ቀደም ሲል ባደረጓቸው ሰባት ጨዋታዎች ሊድስ አምስት ጊዜ ድል ሲቀናው፣ በርንሌይ በአንድ ጨዋታ ብቻ አሸንፎ በቀሪው አንድ ጨዋታ ደግሞ አቻ ተለያይተዋል። በሰባቱ ጨዋታዎች ላይ ሊድስ ዩናይትድ 15 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ በርንሌይ ሰባት ግቦችን አስቆጥሯል። ሁለቱ ቡድኖች በዘንድሮው የውድድር ዓመት በስምንተኛው ሳምንት ተገናኝተው በርንሌይ 2 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ይህም በፕሪሚየር ሊጉ ታሪኩ በሊድስ ላይ ያገኘው ብቸኛ ድል ነው። ሊድስ ዩናይትድ ካሸነፈ ከወራጅ ቀጠና ስፍራ መራቅ የሚያስችለውን ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያገኛል። ለበርንሌይ ጨዋታው ከመርሐ ግብር ማሟያነት የዘለለ ትርጉም የለውም። የዛሬውን ጨዋታ የ36 ዓመቱ ቶም ብራሞል በዋና ዳኝነት እንዲመሩት ተመድበዋል። የ35ኛው ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መርሐ ግብርም እስከ መጪው ሚያዝያ 26 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ይቆያል።
የሳምንቱ ተጠባቂ ጨዋታ፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ ሲዳማ ቡና
May 1, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 23/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 29ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ ስምንት ሰዓት ላይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሲዳማ ቡና በአዲስ አበባ ስታዲየም የሚያደርጉት ጨዋታ የስፖርት ቤተሰቡን ትኩረት ስቧል። በሊጉ ካደረጋቸው 28 ጨዋታዎች መካከል ዘጠኙን ያሸነፈው ቅዱስ ጊዮርጊስ በ11ዱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ስምንት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ28ቱ ጨዋታዎች ላይ 24 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 27 ጎሎች ተቆጥረውበታል። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ35 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በበኩሉ በሊጉ 28 ጨዋታዎችን አከናውኖ 15 ጊዜ ድል ሲቀናው በአራቱ ተሸንፏል። በቀሪ ዘጠኝ ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 35 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 17 ጎሎች ተቆጥሮበታል። ሲዳማ ቡና በ54 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ከቀናት በፊት በ20ኛ ሳምንት የሊጉ ተስተካካይ መርሐ ግብር 3 ለ 1 የተሸነፈው ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ካለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች በአራቱ ድል የቀናው ሲዳማ ቡና ማሸነፍ መሪነቱን እንዲያጠናክር ያስችለዋል። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት የሊጉ ጨዋታ አንድ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከምድረ ገነት ሽሬ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ባህር ዳር ከተማ በ36 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። ምድረ ገነት ሽሬ በ29 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በዘንድሮው ዓመት በሊጉ በርካታ ጨዋታዎች (15 ጊዜ) አቻ የወጣው ባህር ዳር ከተማ ባለፉት ሁለት መርሐ ግብሮች ድል አልቀናውም። ምድረ ገነት ሽሬ ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች ከድል በመራቅ የውጤት ማጣት ቀውስ ይገኛል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ ድል መንገድ ለመመለስ ይፋለማሉ። መቀሌ 70 እንደርታ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት እያደረገ ባለው ፉክክር ሶስት ነጥብ እጅጉን ያስፈልገዋል።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከወራጅ ቀጠና የወጣበትን ድል አስመዘገበ
Apr 30, 2026 219
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 29ኛ ሳምንት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮጵያ ቡናን 4 ለ 2 አሸንፏል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጋናዊው ኮንኮኒ ሃፊዝ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ያሬድ ከበደና በየነ ባንጃ ቀሪዎቹን ጎሎች ለወልዋሎ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አቡበከር አዳሙ እና በረከት ብርሃኑ ለኢትዮጵያ ቡና ጎሎችን አስቆጥረዋል። በሊጉ ስምንተኛ ድሉን ያገኘው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ35 ነጥብ ካለበት 17ኛ ደረጃ ወደ 14ኛ ከፍ በማለት ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ቡና በ41 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ29ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ሀዲያ ሆሳዕና እና መቀሌ 70 እንደርታ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ነገሌ አርሲ ከፋሲል ከነማ እንዲሁም አርባምንጭ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያደረጓቸው ጨዋታዎች ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል።
አርባምንጭ ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያለ ግብ አቻ ተለያዩ
Apr 30, 2026 206
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ):- የአርባምንጭ ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የ29ኛ ሳምንት ጨዋታ ምንም ግብ ሳይቆጠርበት በአቻ ውጤት ተጠናቋል። ጨዋታው በአዲስ አበባ ስታዲየም ተካሄዷል። ውጤቱን ተከትሎ አርባምንጭ ከተማ በ25 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ35 ነጥብ ደረጃውን ከ13ኛ ወደ 11ኛ ከፍ ያደረገ ቢሆን ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም።
ነገሌ አርሲ እና ፋሲል ከነማ ነጥብ ተጋሩ
Apr 30, 2026 147
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ29ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ነገሌ አርሲ እና ፋሲል ከነማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተካሂዷል። ውጤቱን ተከትሎ አዲስ አዳጊው ነገሌ አርሲ በ45 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት አራት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ፋሲል ከነማ በ43 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አምስተኛ ከፍ አድርጓል። ቡድኑ ባለፉት የሊግ ጨዋታዎች ድል አልቀናውም።
ስፖርት ለሰላም ግንባታና ለህዝብ ትስስር መጠናከር ያለውን አስተዋጽኦ ለማጎልበት ይሰራል
Apr 30, 2026 142
ጂንካ፤ ሚያዝያ 22/2018(ኢዜአ)፦ ስፖርት ለሰላም ግንባታና ለህዝብ ትስስር መጠናከር ያለውን አስተዋጽኦ ለማጎልበት እንደሚሰራ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እግር ኳስ ፌዴሬሽን ገለጸ። 3ኛ ዙር የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እግር ኳስ ክለቦች ሻምፒዮና ዛሬ በጂንካ ከተማ ተጀምሯል። በመክፈቻ ሥነ-ስርአቱ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ደመላሽ ይትባረክ እንዳሉት፣ የሻምፒዮና ውድድሩ በክልሉ እግር ኳስ ክለቦች መካከል የሚካሄደው ነው። ሻምፒዮናው ከስፖርታዊ ውድድር ባለፈ የባህል ልውውጥ ለማድረግ እና የእርስ በእርስ ትስስርን ለማጠናከር ትልቅ ሚና እንዳለው አንስተዋል። በመሆኑም ስፖርታዊ ውድድሮች ከመዝናኛነት ባሻገር ለሰላም እሴት ግንባታና ወንድማማችነትን ለማጠናከር ያላቸውን አስተዋጽኦ ለማጠናከር በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የአሪ ዞን ባህልና ስፖርት ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሲሳይ ጋልሺ በበኩላቸው የክለቦች ሻምፒዮናው ለ15 ቀናት የሚካሄድ ነው ብለዋል። በውድድሩም በክልሉ የሚገኙ 18 የወንዶች የእግር ኳስ ክለቦች እና 5 የሴቶች የእግር ኳስ ክለቦች እንደሚሳተፉ አመልክተዋል። በውድድሩ ከ1ኛ እስከ 4ኛ የወጡ ክለቦች በቀጣይ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሚካሄድ የእግር ኳስ ክለቦች ሻምፒና ላይ ክልሉን ወክለው ይሳተፋሉ ብለዋል። ክልሉ የብዝሀ ባህልና እምቅ የቱሪዝም ሀብቶች መገኛ መሆኑን ጠቅሰው፣ ስፖርታዊ ውድድሮች እነዚህን ሀብቶችን ጭምር ለማስተዋወቅ ትልቅ ሚና አላቸው ሲሉ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሪነቱን ያጠናከረበት ድል አስመዘገበ
Apr 30, 2026 104
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ23ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አዲስ አበባ ከተማን 4 ለ 0 ረቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ረድኤት አስረሳኸኝ ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር እሙሽ ዳንኤል እና መሳይ ተመስገን ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ሰናይት ቦጋለ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ 19ኛ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ60 ነጥብ ተመሳሳይ ነጥብ ያለውን ኢትዮ ኤሌክትሪክን በግብ ክፍያ በልጦ መሪነቱን አጠናክሯል። የሁለቱ ቡድኖች የዋንጫ ፉክክር አጓጊ ሆኗል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 18ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዲስ አበባ ከተማ በ11 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች ኢትዮ ኤሌክትሪክ ይርጋጨፌ ቡናን 2 ለ 1፣ ቦሌ ክፍለ ከተማ ድሬዳዋ ከተማን 5 ለ 1 አሸንፈዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 23ኛ ሳምንት ተጠናቋል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Apr 30, 2026 91
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ23ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ይርጋጨፌ ቡናን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ገብርኤላ አበበ እና ብርሃን ኃይለስላሴ የማሸነፊያ ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አዳነች አስፋው የይርጋጨፌ ቡናን ብቸኛ ግብ አስቆጥራለች። ግብ ያስቆጠረችው ገብርኤላ አበበ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ 19ኛ ድሉን ያስመዘገበው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ60 ነጥብ የሊጉን መሪነት በጊዜያዊነት ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተረክቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 14ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ይርጋጨፌ ቡና በ17 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል።
መቀሌ 70 እንደርታ እና ሀድያ ሆሳዕና አቻ ተለያዩ
Apr 30, 2026 80
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በመቀሌ 70 እንደርታ እና በሀዲያ ሆሳዕና መካከል የተደረገው የሊጉ 29ኛ ሳምንት ፍልሚያ በአንድ አቻ ውጤት ተጠናቋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኬኔዲ ገብረጻዲቅ በ49ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ መቀሌ 70 እንደርታን መሪ አድርጓል። መቀሌ 70 እንደርታ ጨዋታውን በድል ያጠናቅቃል ተብሎ ቢጠበቅም፣ በጭማሪ ሰዓት 97ኛው ደቂቃ ፀጋዓብ ግዛው ከመረብ ጋር ያገናኛት ጎል ሀዲያ ሆሳዕና ነጥብ ተጋርቶ እንዲወጣ አስችላለች። የሀዲያ ሆሳዕና የተከላካይ መስመር ተጫዋቾች የሆኑት ዳግም ወንድሙ እና ሄኖክ አርፊጮ መደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በጭማሪ ሰዓት በሁለተኛ ቢጫ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብተዋል። ውጤቱን ተከትሎ መቀሌ 70 እንደርታ በ30 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ትግል ወሳኝ ሶስት ነጥብ ጥሏል። ሀዲያ ሆሳዕና በ35 ነጥብ ከነበረበት 14ኛ ደረጃ ወደ 12ኛ ከፍ ብሏል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም።
ቦሌ ክፍለ ከተማ በድል ጉዞው ቀጥሏል
Apr 30, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት ቦሌ ክፍለ ከተማ ድሬዳዋ ከተማን 5 ለ 1 ረቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ምህረት አየለ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርታለች። ሜላት ጌታቸው እና ትዕግስት ዮሐንስ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ዝናሽ ሰሎሞን የድሬዳዋ ከተማን ብቸኛ ግብ አስቆጥራለች። ሀትሪክ የሰራችው ምህረት አየለ ኮከብ ተጫዋች ሆና ተመርጣለች። በሊጉ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ40 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱም 11ኛ ድሉን አግኝቷል። በሊጉ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና አዲስ አበባ ከተማ የሚያገናኘው መርሐ ግብር ተጠባቂ ነው
Apr 30, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ 9 ሰዓት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከአዲስ አበባ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ57 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። አዲስ አበባ ከተማ በ11 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ መሪነቱን ያጠናክራል። አዲስ አበባ ከተማ በ22ኛ ሳምንት በቦሌ ክፍለ ከተማ 1 ለ 0 ተሸንፏል። ጨዋታውን ማሸነፍ ቡድኑ ላለመውረድ በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከይርጋጨፌ ቡና ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ57 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ይርጋጨፌ ቡና በ17 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ማሸነፍ ኢትዮ ኤሌክትሪክን በዋንጫ ፉክክሩ እንዲቆይ ያደርገዋል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ያሸነፈው ይርጋጨፌ ቡና ከወራጅነት ስጋት ለመላቀቅ ሶስት ነጥብ ያስፈልገዋል። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ቦሌ ክፍለ ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ ይጫወታሉ። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ37 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቦሌ ክፍለ ከተማ ካሸነፈ ተከታታይ ሶስተኛ ድሉን ያስመዘግባል። በአንጻሩ በ22ኛ ሳምንት በይርጋጨፌ ቡና የ1 ለ 0 ሽንፈት ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል።
ነገሌ አርሲ ከፋሲል ከነማ ጋር ይጫወታሉ
Apr 30, 2026 114
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 29ኛ ሳምንት ዛሬ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ነገሌ አርሲ ከፋሲል ከነማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ነገሌ አርሲ በ44 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ በ42 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። አዲስ አዳጊው ነገሌ አርሲ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ፋሲል ከነማ በ28ኛ ሳምንት በመቀሌ 70 እንደርታ የ3 ለ 0 ሽንፈት አስተናግዷል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ቡና ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ቡና በ41 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ32 ነጥብ 17ኛ ደረጃን በበመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ከቀናት በፊት በ20ኛ ሳምንት ተስተካካይ መርሐ ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስን 3 ለ 1 ያሸነፈው ኢትዮጵያ ቡና ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ28ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 2 ለ 0 አሸንፏል። ሁለቱም ቡድኖች በድል ጉዟቸው ለመቀጠል ይፋለማሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አርባምንጭ ከተማ በ24 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ34 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የሊጉ ግርጌ ላይ የሚገኘው አርባምንጭ ከተማ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ ድል መንገድ ለመመለስ ይፋለማሉ። ሀዲያ ሆሳዕና ከመቀሌ 70 እንደርታ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። በ34 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ሀዲያ ሆሳዕና ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ በበኩሉ በ29 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ድል ቀንቶታል። ሀዲያ ሆሳዕና ወደ ድል ለመመለስ፣ መቀሌ 70 እንደርታ ደግሞ የማሸነፍ ጉዞውን አጠናክሮ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት ይጫወታሉ።
አትሌቲኮ ማድሪድ እና አርሰናል አቻ ተለያዩ
Apr 30, 2026 271
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የግማሽ ፍጻሜ መርሐ ግብር አትሌቲኮ ማድሪድ እና አርሰናል ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። በዋንዳ ሜትሮፖሊታኖ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቪክቶር ዮኮሬሽ በ44ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ባስቆጠረው ጎል አርሰናል መሪ ሆኗል። ከእረፍት መልስ ሁሊያን አልቫሬዝ በ56ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት አትሌቲኮን አቻ አድርጓል። በ78ኛው ደቂቃ ኤበሬቺ ኤዘ ላይ በተፈጸመ ጥፋት አርሰናል ያገኘው የፍጹም ቅጣት በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ተሽሯል። የፍጹም ቅጣት ምቱ ውሳኔ መቀልበስ የአርሰናል የቡድን አባላትን ያላስደሰተ ሲሆን ግልጽ የሚያሰጥ ጥፋት ነው በሚል ቅሬታቸውን አሰምተዋል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ሊባል የሚችል ፉክክር ተደርጎበታል። የሁለቱ ቡድኖች የመልስ ጨዋታ በቀጣዩ ሳምንት ማክሰኞ ይደረጋል።
ኢትዮጵያ የዓለም አቀፍ እጅ ኳስ ፌዴሬሽን ትሮፊ 2026 የዞን 5 ውድድርን ታስተናግዳለች
Apr 29, 2026 390
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የ2026 የዓለም አቀፍ እጅ ኳስ ፌዴሬሽን (IHF) ትሮፊ የዞን 5 የምስራቅ አፍሪካ ውድድር ሚያዝያ 26 ቀን 2018 ዓ.ም በኢትዮጵያ አዘጋጅነት በአዲስ አበባ ይካሄዳል። የኢትዮጵያ እና የምስራቅ አፍሪካ እጅ ኳስ ኮንፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ፍትህ ወልደሰንበት (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ውድድሩ ኢትዮጵያን ጨምሮ በ10 ሀገራት መካከል ከ17 ዓመት በታች (Youth) እና ከ19 ዓመት በታች (Junior) ይደረጋል። በውድድሩ ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ ኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ ሩዋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ታንዛኒያ፣ ጅቡቲ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ሶማሊያ እና ሱዳን ይሳተፋሉ። በሁለቱም የዕድሜ ክልል አንደኛ የሚወጡት ሀገራት ቀጥታ ለአህጉራዊው የአፍሪካ ውድድር የሚያልፉ ይሆናል። የውድድሩ ዝግጅት በባህልና ስፖርት ሚኒስቴር፣ በኢትዮጵያ እጅ ኳስ ፌዴሬሽን እና በኢትዮጵያ ኦሎምፒክ ኮሚቴ እየተመራ ሲከናወን የቆየ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ዝግጅቱ መጠናቀቁ ተገልጿል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድኖች ሆቴል ገብተው ዝግጅታቸውን እያደረጉ ይገኛሉ። ቡድኑ እንደ ባለፈው ዓመት አሸናፊ በመሆን ለአፍሪካ ውድድር ለማለፍና ታሪክ ለመሥራት ዝግጁ ነው ሲል የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር መረጃ በመረጃው አመልክቷል። ስፖርታዊ ሁነቱ የኢትዮጵያን የማስተናገድ አቅም የሚያሳይ መሆኑንም ገልጿል።
አዳማ ከተማ እና ድሬዳዋ ከተማ ነጥብ ተጋሩ
Apr 29, 2026 274
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ29ኛ ሳምንት መርሐ ግብር አዳማ ከተማ እና ድሬዳዋ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አቡበከር ሳኒ በ31ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ግብ አዳማ ከተማ መሪ ሆኗል። ከእረፍት መልስ ተቀይሮ የገባው አብዱሰላም ዩሱፍ በ79ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል ለድሬዳዋ ከተማ አንድ ነጥብ አስገኝታለች። ውጤቱን ተከትሎ አዳማ ከተማ በ34 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ዘጠኝ የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ድሬዳዋ ከተማ በ33 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሲሆን ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ በተደረጉ የ29ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች መቻል ኢትዮ ኤሌክትሪክን 1 ለ 0፣ ኢትዮጵያ መድን ሃዋሳ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፈዋል። ሸገር ከተማ እና ወላይታ ድቻ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል።
መቻል ድል ቀንቶታል
Apr 29, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ29ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መቻል ኢትዮ ኤሌክትሪክን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ጋናዊው ኮሊንስ ኮፊ በ61ኛው ደቂቃ ግቧን ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ 12ኛ ድሉን ያስመዘገበው መቻል በ47 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሰባት ዝቅ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ42 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም።
የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን ከወራጅ ቀጠና የወጣበትን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Apr 29, 2026 132
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ29ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን ሃዋሳ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ተባረክ ሄፋሞ በሰባተኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ግብ ሃዋሳ መሪ ሆኗል። አማኑኤል ኤርቦ በ17 እና በ79ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፋቸው ጎሎች ለመድን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አስገኝተዋል። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮጵያ መድን በ34 ነጥብ ደረጃውን ከ17ኛ ወደ 12ኛ ከፍ በማድረግ ከወራጅ ቀጠና ወጥቷል። የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት የሆነው መድን በሊጉ ሰባተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሃዋሳ ከተማ በ43 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ሃዋሳ ከተማ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ባህር ዳር ከተማ ወሳኝ ድል አስመዘገበ
Apr 29, 2026 88
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ23ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ባህር ዳር ከተማ አዳማ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አስቴር ደግአረገ እና ምህረት ታፈሰ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የባህር ዳር ከተማዋ ወርቅነሽ መለሰ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ ስድስተኛ ድሉን ያስመዘገበው ባህር ዳር ከተማ በ19 ነጥብ ከነበረበት 12ኛ ደረጃ ወደ 10ኛ ከፍ ብሏል። ከወራጅ ቀጠና ስፍራ የራቀበትን ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ቡድኑ ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ የ23ኛ ሳምንት ጨዋታ ሃዋሳ ከተማ አርባምንጭ ከተማን 2 ለ 0 ረቷል።
ሃዋሳ ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Apr 29, 2026 151
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 23ኛ ሳምንት ሃዋሳ ከተማ አርባምንጭ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ብርቱካን ገብረክርስቶስ እና የምስራች ላቀው ግቦቹን አስቆጥረዋል። ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሃዋሳ ከተማ በ46 ነጥብ ደረጃውን ከአምስተኛ ወደ አራተኛ ደረጃ ከፍ አድርጓል። በሊጉ 13ኛ ድሉንም አሳክቷል። በውድድር ዓመቱ 17ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት 16 የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀ ሲሆን የመውረዱ ነገር እርግጥ እየሆነ የመጣ ይመስላል።