ቀጥታ፡
ስፖርት
ወላይታ ድቻ ድል ሲቀናው ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ኢትዮጵያ መድን ነጥብ ተጋርተዋል 
Apr 20, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ጨዋታዎች መካሄዳቸውን ቀጥለዋል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው መርሐ ግብር ወላይታ ድቻ ምድረ ገነት ሽሬን 1 ለ 0 ረትቷል። ያሬድ ዳርዛ በ64ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉን ያስመዘገበው ወላይታ ድቻ በ34 ነጥብ ደረጃውን ከ16ኛ ወደ 10ኛ ከፍ አድርጓል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ምድረ ገነት ሽሬ በ29 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች ከድል በመራቅ የውጤት ማጣት ቀውስ ውስጥ ይገኛል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው ጨዋታ ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ ተለያይተዋል።   በዛብህ መለዮ በ67ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ግብ ኢትዮ ኤሌክትሪክ መሪ ሆኗል። ይሁንና አማኑኤል ኤርቦ በ84ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል ለኢትዮጵያ መድን አንድ ነጥብ አስገኝታለች። ሀሰን ሁሴን ከኢትዮ ኤሌክትሪክ፣ አብዱል ጋንዩ ከኢትዮጵያ መድን በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥተዋል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ42 ነጥብ ደረጃውን ከስድስተኛ ወደ አምስተኛ ከፍ አድርጓል። ኢትዮጵያ መድን በ31 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን ባለፉት አራት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። በተመሳሳይ ዛሬ በተደረገ የ28ኛ ሳምንት ጨዋታ ሸገር ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል።
በሐረሪ ክልል ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የሚያስችሉ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ ነው
Apr 20, 2026 175
ሐረር ፤ሚያዚያ 12/2018 (ኢዜአ) ፡-በሐረሪ ክልል በስፖርት ዘርፍ በሚከናወኑ ስራዎች ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ምቹ ሁኔታ እየተፈጠሩ መሆኑን የስፖርት ቤተሰቦች ገለጹ። በክልሉ ‎የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ልማትና የፕሮጀክት ስልጠናዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑ ተመላክቷል ።   በክልሉ የሐረር ጀጎል እግር ኳስ ክለብ አሰልጣኝ አክረም መሀመድ ለኢዜአ እንደገለጸው በክልሉ ከዚህ ቀደም ተተኪ ስፖርተኞችን የማፍራትና የድጋፍና እገዛ ተግባራት ትኩረት ተነፍጎት ቆይቷል። በአሁኑ ወቅት ህፃናትና ታዳጊዎች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ጠቁሞ ለዘርፉ ስልጠና የተሰጠው ትኩረት አሰልጣኞችንም እያበረታታ መሆኑን አመልክቷል ። በክልሉ እየተከናወኑ ያሉ የስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታና የድጋፍ ስራዎች ተሰጥኦ ያላቸው ታዳጊዎችን ወደ ስፖርቱ ለመምጣት ምቹ ሁኔታ እየፈጠሩ ነው ያሉት ደግሞ የታዳጊ ፕሮጀክት እግር ኳስ አሰልጣኝ ኢንስፔክተር ፈይሰል መሀመድ ናቸው።   በተለይ ቀደም ሲል እንደ ችግር ሆኖ ጥያቄ ሲቀርብባቸው የነበሩ ተቀራርቦ የመስራት ተግዳሮቶችን ለመፍታት በተከናወኑ ተግባራት ውጤት እየተገኘ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህም የቅንጅት ስራዎች እየጎለበቱ በመሆኑ ተተኪ ስፖርተኞችን የማፍራት ተግባራትን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ አመላክተዋል። የታዳጊ ፕሮጀክት ሰልጣኝ የሆነው ማስተዋል ታጠቅ በበኩሉ “በከተማው ከኮሪደር ልማት ጋር በማስተሳሰር በየአካባቢው የተከናወኑ የስፖርት ማዘወተሪያ ስፍራዎች ተሰጧችንን ለማውጣት እድል እየፈጠሩልን ነው ብሏል። በተለይ በታዳጊዎች ፕሮጀክት ታቅፈን የሚሰጠን ስልጠና ወደፊት ታላላቅ ክለቦች ላይ መሳተፍ የሚያስችለን ክህሎት እየወሰድን እንገኛለን ፤ እኛም ደግሞ በተገቢው መንገድ እየሰራን እንገኛለን ሲል ገልጿል።   በክልሉ ለታዳጊ ፕሮጀክት ስልጠና እየተደረገ የሚገኘው ድጋፍና በየአካባቢው የስፖርት ማዘውተርያ ስፍራ ግንባታ ተስፋ የሚሰጡ ስራዎች ሆነው አግኝተናቸዋል ያለው ሌላው የታዳጊ ፕሮጀክት ሰልጣኝ አብረሃም አሸናፊ ነው። እኛም የነገዋ ኢትዮጵያ የምትጠብቅብንን አሸናፊነት ለማምጣት ከወዲሁ ተግተን እየሰራን እንገኛለን ብሏል የሐረሪ ክልል ስፖርት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙራድ አብዲ በበኩላቸው በክልሉ ‎የስፖርት ማዘውተሪያ ስራዎችን የማልማትና ፋሲሊቲዎችን በማሟላት ተተኪ ስፖርተኞችን የማፍራት ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ነው ብለዋል።   በዚህም የክልሉ መንግስት ቀደም ሲል የነበሩ የማዘውተርያ ስፍራዎችን የማዘመን እንዲሁም በየወረዳው አንድ የስፖርት ማዘውተርያ ስፍራ የመገንባት ስራ በእቅድ ይዞ እያከናወነ ይገኛል ሲሉ ተናግረዋል። እግር ኳስን ጨምሮ በሁሉም የስፖርት ዓይነቶች ክልሉን ብሎም ሀገርን ወክለው በዓለም አቀፍ መድረክ የሚወዳደሩ ስፖርተኞችን ማፍራት የሚያስችሉ የታዳጊ ፕሮጀክት ስልጠናዎች አዲስ ፎርማት ተቀርጾላቸው ስልጠና እየተሰጠ መሆኑን አመልክተዋል።  
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን 29ኛው ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ መካሄድ ጀመረ
Apr 20, 2026 102
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን 29ኛው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ዛሬ በአዲስ አበባ ማካሄድ ጀምሯል። እስከ ነገ ድረስ በሚቆየው በዚህ ጉባኤ ላይ የ2017 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ውይይት ተደርጎበት ጸድቋል። ጉባኤው የውጭ ኦዲተርን የመሰየም እንዲሁም የ2017 በጀት ዓመት የውጭ ኦዲት ሪፖርትን በማዳመጥ ተወያይቶ የማጽደቅ አጀንዳዎችን ይዟል።   በተጨማሪም የ2018 በጀት ዓመት የሥራ ዕቅድና በጀት ላይ በመምከር ውሳኔ የሚያሳልፍ ይሆናል። ሌላው በጉባኤው የሚዳሰሰው ጉዳይ ተቋማዊ አሰራር (ሪፎርም) ሰነድ እና የሰው ኃይል መዋቅራዊ ጥናትን ተመልክቶ ማጽደቅ ሲሆን፣ የተሻሻለውን የፌዴሬሽኑ መተዳደሪያ ደንብም መርምሮ ያጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል። ጉባኤው የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድን እንዲሁም የተሻሻለውን የፌዴሬሽኑ የግዥ፣ ፋይናንስና ንብረት አስተዳደር መመሪያን በአጀንዳነት በመያዝ ውይይት በማድረግ እንደሚያጸድቅ የፌዴሬሽኑ መረጃ ያመለክታል።
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
Apr 20, 2026 115
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ ግብር ዛሬ በክሪስታል ፓላስ እና ዌስትሃም ዩናይትድ መካከል ይካሄዳል። ጨዋታው ምሽት 4 ሰዓት ላይ በሰልኸረስት ፓርክ ስታዲየም ይካሄዳል። ክሪስታል ፓላስ በ42 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዟል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ32 ነጥብ 17ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ክለቦች በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሲገናኙ የአሁኑ ለ35ኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው 34 ጨዋታዎች ክሪስታል ፓላስ በ13ቱ ሲያሸንፍ ዌስትሃም በ11ዱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ 10 ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርተዋል። በ34ቱ ጨዋታዎች ክሪስታል ፓላስ 52 ግቦችን ሲያስቆጥር፣ ዌስትሃም ዩናይትድ 50 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ቡድኖቹ ባለፉት አምስት የሊግ ግንኙነታቸው ፓላስ ሶስት ጊዜ ሲያሸንፍ ዌስትሃም አንድ ጊዜ ድል ቀንቶታል። በቀሪ አንድ ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት በአምስተኛ ሳምንት በለንደን ስታዲየም ተገናኝተው ክሪስታል ፓላስ 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። በ32ኛ ሳምንት ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 1 ያሸነፈው ክሪስታል ፓላስ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። በተመሳሳይ በ32ኛ ሳምንት ዎልቭስን 4 ለ 0 የረታው ዌስትሃም ዩናይትድ ከወራጅ ቀጠናው ለመራቅ ሶስት ነጥብ ማግኘት ወሳኝ ነው። ሁለቱ የለንደን ክለቦች በጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ያሳያሉ ተብሎ ይጠበቃል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት የሶስተኛ ቀን ውሎ 
Apr 20, 2026 88
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይከናወናሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከኢትዮጵያ መድን በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ41 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ መድን በ30 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ27ኛ ሳምንት አዳማ ከተማን 1 ለ 0 ያሸነፈው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በድል ጉዞው ለመቀጠል ይጫወታል። የወቅቱ የሊጉ የዋንጫ ባለቤት ኢትዮጵያ መድን ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። መድን ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት የሚያስችለውን ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በሌላኛው መርሐ ግብር ባህር ዳር ከተማ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባህር ዳር ከተማ በ36 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። ሸገር ከተማ በ32 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ27ኛ ሳምንት ከኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ የተለያየው ባህር ዳር ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በበርካታ ጨዋታዎች (15 ጊዜ) አቻ የወጣ ቡድን ነው። ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች ያላሸነፈው አዲስ አዳጊው ሸገር ከተማ ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና አካባቢ እንዲርቅ ያስችለዋል። ምድረ ገነት ሽሬ ከወላይታ ድቻ ከቀኑ 10 ሰዓት በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረ ገነት ሽሬ በ29 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ወላይታ ድቻ በ31 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ምድረ ገነት ሽሬ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ትግል ሶስት ነጥብ ማግኘት ግድ ይለዋል። በ27ኛ ሳምንት በፋሲል ከነማ 1 ለ 0 የተሸነፈው ወላይታ ድቻ ወደ አሸናፊነት መንገድ ለመመለስ ይጫወታል።
ሲዳማ ቡና የሊጉን መሪነት ያጠናከረበት ወሳኝ ድል አስመዘገበ
Apr 19, 2026 561
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11 /2018 (ኢዜአ)፦‎ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ28ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ አቤል ያለው ግቦቹን አስቆጥሯል።   በሊጉ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በ54 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ መቻል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ 10 ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ32 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። የሲዳማ ቡናው አቤል ያለው በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ 14 ከፍ በማድረግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት መሪነቱን አጠናክሯል።   በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር መቻል እና ሃዋሳ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። መቻል በ44 ነጥብ ሁለተኛ፣ ሃዋሳ ከተማ በ43 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዘዋል።   ነገሌ አርሲ ከሀድያ ሆሳዕና አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኪቲካ ጅማ ለነገሌ አርሲ፣ ተመስገን ብርሃኑ ለሀድያ ሆሳዕና ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ውጤቱን ተከትሎ ነገሌ አርሲ በ44 ነጥብ ሶስተኛ፣ ሀድያ ሆሳዕና በ34 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ዛሬ በአዲስ አበባ ስታዲየም አስቀድሞ የተካሄደው የኢትዮጵያ ቡና እና አርባምንጭ ከተማ ጨዋታ አንድ አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል። ቢንያም ጌታቸው ለኢትዮጵያ ቡና፣ ይድነቃቸው ያሲን ለአርባምንጭ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ኢትዮጵያ ቡና በ38 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ24 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ዘመናዊ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ለአፍሪካ አርአያ ናቸው
Apr 19, 2026 790
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ዘመናዊ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ለቀሪዎቹ አፍሪካ ሀገራት ትልቅ ተምሳሌት ያለው በመሆኑ ተሞክሮውን ሊቀስሙ ይገባል ሲሉ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት አትሌቶች ገለጹ። በአዲስ አበባ ለመጀመሪያ ጊዜ በተካሄደው የ2026 ዓለም አቀፍ የአንድ ቀን የግራንድ ፕሪክስ ውድድር ላይ የተሳተፉ ስመ ጥር አትሌቶች፣ በከተማዋ የተገነቡ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ጎብኝተዋል።   አትሌቶቹ የዓድዋ ድል መታሰቢያን፣ የአዲስ ስፖርት ፓርክን እና የወንዝ ዳርቻ ልማትን ተዘዋውረው የተመለከቱ ሲሆን፤ በተገነቡት መሠረተ ልማቶች ጥራትና ውበት መደነቃቸውን ገልጸዋል። በተለይም ኢትዮጵያ ለአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት መሆኗን ያስታወሱት አትሌቶቹ፣ በታሪካዊቷ ከተማ አዲስ አበባ በመገኘታቸው ላቅ ያለ ኩራት እንደተሰማቸው በአጽንኦት ገልጸዋል። የዚምባብዌ አትሌት አሽሊ ቲናሼ ሚለር፤ የታላላቅ አትሌቶች መፍለቂያ በሆነችው ኢትዮጵያ፣ መንግስት ለስፖርቱ ዘርፍ የሰጠው ትኩረት እጅግ የሚያስደስት እና ለሌሎች ሀገራት ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን ተናግራለች።   የቦትስዋናው አትሌት ሌትልሆጎኖሎ ሞክጌቲ ፤የስፖርት ማዘውተሪያዎቹ ዘመናዊና የተሟላ ግብዓት ያላቸው መሆናቸው ቀልቡን እንደሳበው በመግለጽ፣ እንዲህ ያሉ መሰረተ ልማቶች የአፍሪካ አትሌቶች በዓለም አቀፍ መድረክ ተወዳዳሪነታቸውን ለማሳደግ ወሳኝ እንደሆኑ ተናግሯል።   የሴኔጋል አትሌት ሩጊ ሶው፤ በኢትዮጵያ የታዩት የስፖርት መሠረተ ልማቶች ዘመናዊና አቅምን የሚያሳድጉ በመሆናቸው፣ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በሞዴልነት ሊወሰዱ እንደሚችሉ አስረድታለች።   የኬንያ አትሌት ፓሊን ሙርጋ፤ እንዲህ ያሉ ድንቅ የስፖርት ማዘውተሪያዎች በየስፍራው ሊገነቡ እንደሚገባ አመልክታ በዚህም የሀገርን ገጽታ በስፖርት መገንባት እንደሚቻል ገልጻለች።     በአጠቃላይ አትሌቶቹ፣ በከተማ ልማትና በስፖርት መሠረተ ልማት ረገድ ኢትዮጵያ እያሳየችው ያለው ፈጣን ለውጥ ለቀጣዩ የአፍሪካ ትውልድ ትልቅ ተስፋ የሚሰጥ መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይም በአዲስ ስፖርት ፓርክ ውስጥ ሀውልት የቆመላቸውን ታዋቂ አትሌቶች በመመልከት ወጣቱ ትውልድ "እኔስ መቼ ነው የሀገሬን ስም በዓለም አደባባይ የማስጠራው" የሚል በጎ የቁጭት ስሜት እንዲያድርበትና ለላቀ ስኬት እንዲነሳሳ የሚያደርግ መሆኑም አትሌቶቹ ተናግረዋል።
የዋንጫውን መዳረሻ ይወስናል በተባለው ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ አርሰናልን አሸነፈ
Apr 19, 2026 158
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር ማንችስተር ሲቲ አርሰናልን 2 ለ 1አሸንፏል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ራያን ቸርኪ እና አርሊንግ ሃላንድ ለውሃ ሰማያዊዎቹ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ካይ ሃቫርትዝ ለአርሰናል ብቸኛውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በጨዋታው ማንችስተር ሲቲ የተሻለ ብልጫ ነበረው። አርሰናል በጨዋታው ያገኛቸውን ግልጽ የግብ እድሎች አልተጠቀመም።   በሊጉ 20ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ሲቲ በ67 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው ከሊጉ መሪ አርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሶስት ዝቅ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርሰናል በ70 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የዛሬው ውጤት በሁለቱ ክለቦች መካከል ያለውን የዋንጫ ፉክክር ይበልጥ አጓጊ አድርጎታል። ዛሬ በተደረጉ ሌሎች ጨዋታዎች በመርሲሳይድ ደርቢ ሊቨርፑል ኤቨርተንን 2 ለ 1 አሸንፏል። አስቶንቪላ ሰንደርላንድን 4 ለ 3፣ ኖቲንግሃም ፎረስት በርንሌይን 4 ለ 1 አሸንፈዋል። የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ነገ ክሪስታል ፓላስ ከዌስትሃም ዩናይትድ በሚያደርጉት ጨዋታ ይጠናቀቃል።
የመዲናዋ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ዓለም አቀፍ ውድድሮችን የማስተናገድ ደረጃ ላይ መድረሳችንን ያሳያሉ-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 19, 2026 589
አዲስ አበባ፣ሚያዚያ 11/ 2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ ከተማ የተገነቡ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ውድድሮችን የማስተናገድ ደረጃ ላይ መድረሳችንን የሚያሳዩ ናቸው ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፡፡ ከንቲባ አዳነች በአዲስ አበባ የተገነቡ ዘመናዊ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ውጤት ኢትዮጵያ በአትሌቲክስ ዘርፍ ያላትን ታላቅ ዝና ዳግም ለማረጋገጥ እድል የሰጠ ነው ብለዋል፡፡   የተገነቡት የስፖርት መሰረተ ልማቶች መዲናችን ማንኛውንም ዓይነት ዓለም አቀፍ ውድድር የማስተናገድ ብቃትና ደረጃ ላይ መድረሷን የሚያሳዩ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በአዲስ አበባ የሚከናወኑ ውድድሮች ተተኪ አትሌቶችን ከማነቃቃት ባለፈ ለስፖርት ቱሪዝም ዕድገት የጎላ ፋይዳ እንዳላቸው አስረድተዋል፡፡   ከተማዋን ለነዋሪዎቿ ምቹና ሳቢ ከማድረግ ባሻገር ለዓለም አቀፍ ኩነቶች የስበት ማዕከል መሆኗን በተግባር ማሳየት ተችሏል ነው ያሉት ከንቲባዋ፡፡ ዓለም አቀፍ እና አህጉር አቀፍ መድረኮችን ማዘጋጀት ሀገራዊ አንድነትን በማጠናከር ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለውም አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡
የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ውድድሮችን የማስተናገድ ብቃቷን ያሳየችበት መድረክ ነው
Apr 19, 2026 320
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድር ኢትዮጵያ ግዙፍ ስፖርታዊ ኹነቶችን የማስተናገድ አቅምና ብቃት እንዳላት በተግባር ያሳየችበት መድረክ መሆኑን የኢትዮጵያ ዝነኛ አትሌቶች ገለጹ። ኢትዮጵያ በ2027 የዓለም አትሌቲክስ የወርቅ ደረጃ ውድድርን እንድታስተናግድ ዕድል በማግኘቷ ደስታ እንደተሰማቸውም ጠቅሰዋል። የዓለም አትሌቲክስ የአንድ ቀን ውድድር የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ ስታዲየም ትላንት በስኬት ተካሂዷል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ምክትል ፕሬዚዳንት አትሌት መሰረት ደፋር እንደገለጸችው፣ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ለበርካታ ዓመታት በተለያዩ የዓለም ሀገራት በመዘዋወር ሲወዳደሩ ቆይተዋል።   እንዲህ ያሉ ውድድሮች በሀገራችን እንዲካሄዱ የነበረው ምኞት ዛሬ እውን በመሆኑ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማት ተናግራለች። የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ውድድር መካሄዱ ለአትሌቶቻችን ትልቅ መነቃቃትን ፈጥሯል ነው ያለችው። ኢትዮጵያ ማንኛውንም ዓለም አቀፍ የውድድር መድረክ በብቃት ማስተናገድ እንደምትችል ለዓለም ያስመሰከረችበት መሆኑንም አትሌት መሠረት ገልጻለች። በተመሳሳይ ታዋቂው አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ውድድሮች እንዲኖሯት የሁልጊዜ ምኞቱ መሆኑን ያስታውሳል።   የዓለም አትሌቲክስ የአንድ ቀን ውድድር የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ መካሄዱ የረጅም ጊዜ ህልሙን ያሳካ መሆኑን ገልጿል። ኢትዮጵያ ውድድሩን በስኬት ማስተናገዷ ለሀገር ትልቅ ኩራት መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ኢንጅነር ጌቱ ገረመው ናቸው። ከዚህም ባለፈ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሌሎች ውድድሮችን ለማስተናገድ በር የከፈተና ሀገራችን ትልቅ አመኔታ እንድታገኝ ያደረገ መሆኑን አንስተዋል።   በቀጣይ የተሻሉ ዕድሎችን ለመጠቀም በስፖርት መሰረተ ልማትና በዝግጅት ረገድ ጠንክሮ መስራት እንደሚገባ አመላክተዋል። አትሌት መሰረት ደፋር እና አትሌት ቀነኒሳ በቀለ፣ መንግሥት ኢትዮጵያ በአትሌቲክስ ያላትን ገናና ስም ለማስቀጠል ለዘርፉ ለሰጠው ትኩረት ምስጋና አቅርበዋል። የተጀመሩ የስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉም ጠይቀዋል። በታሪካዊው የአዲስ አበባ ግራንድ ፕሪክስ ውድድር ላይ ከ70 በላይ ዓለም አቀፍ አትሌቶች ተሳታፊ መሆናቸው ታውቋል።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከድሬዳዋ ከተማ ይጫወታል 
Apr 19, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ዛሬ አራት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ሲዳማ ቡና ድሬዳዋ ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና በ51 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ድሬዳዋ በ32 ነጥብ 15ኛ ይዟል። በ27ኛው ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 1 ለ 0 የረታው ሲዳማ ማሸነፍ መሪነቱን እንዲያጠናክር ያስችለዋል። በመቻል በ27ኛው ሳምንት 2 ለ 1 የተሸነፈው ድሬዳዋ ከተማ ወደ ድል መንገድ ለመመለስ ይጫወታል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ መቻል ከሃዋሳ ከተማ በሃዋሳ ዩኒቨርሲቲ የሚያደርጉት ጨዋታ የሚጠበቅ ነው። መቻል በ43 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሃዋሳ ከተማ በ42 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። በጥሩ ወቅታዊ ብቃት ላይ የሚገኘው መቻል ማሸነፍ በድል ጉዞው እንዲቀጥል ከማስቻሉ ባሻገር ወደ በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። ባለፉት አራት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ በበኩሉ በዋንጫ ፉክክሩ ለመቆየት ማሸነፍ ግድ ይለዋል። በሌላኛው መርሐ ግብር ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ነገሌ አርሲ ከሀድያ ሆሳዕና በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ነገሌ አርሲ በ43 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟልል። ሀድያ ሆሳዕና በ33 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አቻ የወጣው ነገሌ አርሲ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ማሸነፍ በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በ27ኛ ሳምንት ከኢትዮጵያ ቡና ጋር ሁለት አቻ የወጣው ሀድያ ሆሳዕና ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። ኢትዮጵያ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አንድ ተስተካካይ ጨዋታ የሚቀረው ኢትዮጵያ ቡና በ37 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ23 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ሁለቱ ቡድኖች በተመሳሳይ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፉም። ቡድኖቹ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ጨዋታ ተመጣጣኝ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከደቡብ ሱዳን ጋር ይጫወታል 
Apr 19, 2026 84
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በ10ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የአፍሪካ ዞን ቅድመ ማጣሪያ ኢትዮጵያ የመልስ ጨዋታዋን ዛሬ ከደቡብ ሱዳን ጋር ታደርጋለች። ጨዋታው ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳል። ሁለቱ ሀገራት ሚያዚያ 4 ቀን 2018 ዓ.ም በጁባ ስታዲየም ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ በቤተልሔም ግዛቸው እና ምኀረት አየለ ጎሎች 2 ለ 0 አሸንፋለች። በራውዳ አሊ የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ወደ ቀጣዩ ዙር የማለፍ እድሉን አስፍቷል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከጁባ ከተመለሰ በኋላ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ዝግጅቱን ሲያደርግ መቆየቱንና ትናንት ደግሞ የመጨረሻ ልምምዱን ማከናወኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በሞሰስ ዛካሪያ ንጎር የሚሰለጥነው የደቡብ ሱዳን ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከትናንት በስቲያ አዲስ አበባ የገባ ሲሆን የመጨረሻ ልምምዱንም ትናንት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም አከናውኗል። ኢትዮጵያ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈች በሁለተኛው ዙር ከብሩንዲ ጋር ትጫወታለች። ትናንት በተደረገ የመልስ ጨዋታ ብሩንዲ ማላዊን 2 ለ 1 በማሸነፍ በአጠቃላይ ድምር ውጤት ተጋጣሚዋን 4 ለ 2 በመርታት ወደ ሁለተኛው ዙር አልፋለች። 10ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት ሴቶች የዓለም ዋንጫ በሞሮኮ አስተናጋጅነት ከጥቅምት 7 እስከ ጥቅምት 28 ቀን 2019 ዓ.ም ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። በማጣሪያ የሚያልፉ አራት የአፍሪካ ሀገራት በሶስት ዙሮች በሚደረጉ ጨዋታዎች ይለያሉ።
ማንችስተር ሲቲ ከአርሰናል ፦ የዋንጫው ዕጣ ፈንታ የሚወሰንበት ታላቅ ፍልሚያ
Apr 19, 2026 185
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ማንችስተር ሲቲ ከአርሰናል የሚያደርጉት ጨዋታ የዓለም እግር ኳስ አፍቃሪያንን ቀልብ ስቧል። ጨዋታው ምሽት 12 ሰዓት ከ30 ላይ በኢትሃድ ስታዲየም ይካሄዳል። ማንችስተር ሲቲ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው በ64 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አርሰናል በ70 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ሁለቱ ክለቦች በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሲገናኙ የአሁኑ ለ58ኛ ጊዜ ነው።   ከዚህ ቀደም በነበራቸው 57 የሊግ ግንኙነት አርሰናል 25ቱን በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። ማንችስተር ሲቲ 19 ጊዜ ድል ሲቀናው በቀሪ 13 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። በ57ቱ ጨዋታዎች አርሰናል 82 ግቦችን ሲያስቆጥር፣ ማንችስተር ሲቲ 75 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል።   ቡድኖቹ ባለፉት 10 የሊግ ግንኙነታቸው ሲቲ አምስት ጊዜ ሲያሸንፍ አርሰናል በሁለቱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርተዋል። በዘንድሮው የውድድር ዓመት በአምስተኛ ሳምንት በኤምሬትስ ስታዲየም ባደረጉት የሊግ ጨዋታ አንድ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በ32ኛ ሳምንት አርሰናል በቦርንማዝውዝ 2 ለ 1 መሸነፉና ማንችስተር ሲቲ ቼልሲን 3 ለ 0 ማሸነፉ የዋንጫው ፉክክር ላይ ዳግም ነፍስ ዘርቷል። ባለሜዳው ማንችስተር ሲቲ የዛሬውን ጨዋታ ማሸነፍ አንድ ተስተካካይ ጨዋታ እየቀረው ከአርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ሶስት ዝቅ እንዲያደርግ ያስችለዋል። አርሰናል ድል ከቀናው ዋንጫ የማንሳት እድሉ የበለጠ ሰፊ ይሆናል። ይህ የማንችስተር ሲቲ እና የአርሰናል ግጥሚያ በብዙዎች ዘንድ 'የዘንድሮውን የፕሪሚየር ሊጉ ዋንጫ መዳረሻን የሚበይን' ታላቅ ፍልሚያ ተብሎ ተፈርጇል። የ47 ዓመቱ አንቶኒ ቴይለር ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። በሌሎች ጨዋታዎች ኤቨርተን ከሊቨርፑል ከቀኑ 10 ሰዓት በሂል ዲኪንሰን ስታዲየም የሚያደርጉት የደርቢ ጨዋታ ይጠበቃል። አስቶንቪላ ከሰንደርላንድ እና ኖቲንግሃም ፎረስት ከበርንሌይ በተመሳሳይ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ሪያል ሶሲዬዳድ የኮፓ ዴል ሬይ ዋንጫን ለአራተኛ ጊዜ አነሳ
Apr 19, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በስፔን የኮፓ ዴል ሬይ የፍጻሜ ጨዋታ ሪያል ሶሲዬዳድ አትሌቲኮ ማድሪድን በመለያ ምት አሸንፏል። በሲቪያ ላ ካርቱጃ ስታዲየም በተካሄደው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በ90 ደቂቃ አትሌቲኮ ማድሪድ እና ሪያል ሶሲዬዳድ ሁለት አቻ ተለያይተዋል።   አዴሞላ ሉክማን እና ጁሊያን አልቫሬዝ ለአትሌቲኮ ማድሪድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አንደር ባሬኔትክሲያ በጨዋታ እና ማይክል ኦያርዛባል በፍጹም ቅጣት ምት ለሪያል ሶሲዬዳድ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።   በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ክለቦቹ አቻ በመለያየታቸው 30 ደቂቃ ተጨምሯል። በጭማሪ ሰዓት ግብ ባለመቆጠሩ ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቷል። ሪያል ሶሲዬዳድ በመለያ ምት 4 ለ 3 በማሸነፍ የስፔን ኮፓ ዴል ሬይን (የንጉሱ ዋንጫ) ለአራተኛ ጊዜ አንስቷል።   የባስኩ ክለብ ከአምስት ዓመታት በኋላ የውድድሩ አሸንፏል። አትሌቲኮ ማድሪድ ከ13 ዓመታት በኋላ የኮፓ ዴል ሬይን ዋንጫ የማንሳት ህልሙ አልተሳካም። የማድሪዱ ክለብ 10 ጊዜ ውድድሩን አሸንፏል።
ማንችስተር ዩናይትድ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Apr 19, 2026 120
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ማንችስተር ዩናይትድ ቼልሲን 1 ለ 0 አሸንፏል። በስታምፎርድ ብሪጅ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ማትያስ ኩንሃ በ43ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ባለሜዳው ቼልሲ በርካታ የግብ እድሎችን ቢፈጥርም መጠቀም አልቻለም። በሁለት አጋማሽ የግብ ቋሚ እና አግጣሚ የገጨባቸው አጋጣሚዎች ተጠቃሽ ናቸው።   ዩናይትድ በጨዋታው ያገኘውን ግልጽ የግብ እድል በመጠቀም አሸንፏል። በሊጉ 16ኛ ድሉን ያስመዘገበው ማንችስተር ዩናይትድ በ58 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ዩናይትድ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመሳተፉ ነገር እውን ሊሆን ተቃርቧል። በውድድር ዓመቱ 11ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቼልሲ በ48 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ተሸንፏል።   የዛሬው ሽንፈት ቼልሲ በሻምፒዮንስ ሊጉ የመሳተፍ እድሉን ይበልጥ የጠበበ አድርጎታል። በጨዋታው ለግቡ መቆጠር ምክንያት የሆነው ብሩኖ ፈርናንዴዝ በሊጉ ለ18ኛ ጊዜ ለጎል የሚሆን ኳስ አመቻችቶ አቀብሏል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም