ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
የሊጉ መሪ ሲዳማ ነጥብ ጣለ
Jan 8, 2026 16
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ሲዳማ ቡና እና አርባምንጭ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተደርጓል። ውጤቱን ተከትሎ የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ነጥቡን ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ነጌሌ አርሲ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ለማስፋት ያገኘውን እድል አልተጠቀመም። አርባምንጭ ከተማ በስምንት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ እስከ አሁን ምንም ጨዋታ ያላሸነፈ ብቸኛ ቡድን ነው። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሃ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከአዳማ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ኪሩቤል ወንድሙ ለወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በጨዋታ እና ቢኒያም አይተን በፍጹም ቅጣት ለአዳማ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በ14ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ነጌሌ አርሲ ምድረ ገነት ሽሬን 1 ለ 0 አሸንፏል።
ነጌሌ አርሲ ተከታታይ አራተኛ ድሉን አስመዘገበ
Jan 8, 2026 59
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ነጌሌ አርሲ ምድረ ገነት ሽሬን 1 ለ 0 አሸንፏል። የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ጋር ይጫወታል አሁናዊ ቁጥራዊ መረጃዎች ስለ 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ከቤ ብዙነህ በ12ኛው ደቂቃ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በሊጉ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘገበው ነጌሌ አርሲ በ25 ነጥብ ደረጃውን ከሶስተኛ ወደ ሁለተኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉ አምስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ምድረ ገነት ሽሬ በ17 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። የማድሪድ ደርቢ በስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ አርሰናል እና ሊቨርፑል የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
አሁናዊ ቁጥራዊ መረጃዎች ስለ 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ
Jan 8, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 30/2018(ኢዜአ)፦በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ወደ ሩብ ፍጻሜው ተሸጋግሯል። በውድድሩ እስከ አሁን በተደረጉ 44 ጨዋታዎች 87 ግቦች ከመረብ ላይ አርፈዋል። ይህም በአማካይ በአንድ ጨዋታ 1 ነጥብ 98 ጎል ይቆጠራል ማለት ነው። ናይጄሪያ 12 ግቦችን በውድድሩ ላይ በማስቆጠር ቀዳሚውን ስፍራ የያዘች ሀገር ናት። በተጨማሪም 64 የግብ ሙከራዎች (30 ኢላማቸውን የጠበቁ) ሙከራዎችን በማድረግ ከፍተኛውን ድርሻ ይዛለች። በተጨማሪም ናይጄሪያ በየጨዋታው የ66 በመቶ የኳስ ድርሻ በመያዝ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ከፍተኛውን ድርሻ የያዘች ሀገር ሆናለች። ቦትስዋና፣ ጋቦን እና ዩጋንዳ በተመሳሳይ ሰባት ጎሎችን በማስተናገድ በርካታ ግብ የተቆጠረባቸው ሀገር መሆናቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል። የሞሮኮው ብራሂም ዲያዝ አራት ግቦችን በማስቆጠር የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ነው። የናይጄሪያው አዴሞላ ሉክማን አራት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል በርካታ የግብ እድሎችን ፈጥሯል። እስከ አሁን በተደረጉ 44 ጨዋታዎች 173 ቢጫ ካርድ እና ሰባት ቀይ ካርዶች ተመዝግበዋል። ከነዚህም ውስጥ ማሊ 11 ቢጫ እና ሁለት ቀይ ካርዶችን በመመልከት የቀዳሚውን ስፍራ ይዛለች። ማሊ እና ቱኒዚያ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ በተመሳሳይ ሁለት የፍጹም ቅጣት ምቶችን በማግኘት በግንባር ቀደምትነት ይቀመጣሉ። የአዘጋጇ ሞሮኮ ተጫዋቾች እስከ አሁን ባደረጓቸው ጨዋታዎች 77 ጊዜ ጥፋት በመፈጸም ጥሩ ያልሆነ ክብረ ወሰን ይዘዋል። የሞሮኮ እና የደቡብ አፍሪካ ተጫዋቾች በተመሳሳይ 10 ጊዜ ከጨዋታ ውጪ በመሆን ብዙ ጊዜ ከጨዋታ ውጪ የሆኑ ተጫዋቾችን የያዙ ሀገራት ሆነዋል። የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ መርሃ ግብር ጥር 1 እና 2 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። አጠቃላይ ውድድሩም እስከ ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በቀሪ ስምንት ጨዋታዎች በአሃዛዊ መረጃዎች ላይ ለውጦች እንደሚኖሩ ይጠበቃል።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ጋር ይጫወታል
Jan 8, 2026 98
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ14ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ በሚደረጉ ጨዋታዎች ይጀመራል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ጨዋታውን ያደርጋል። ሲዳማ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው 13 ጨዋታዎች መካከል ስምንቱን ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በአራት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ13ቱ ጨዋታዎች ላይ 18 ጎሎችን ሲያስቆጥር ስድስት ጎሎች ተቆጥረውበታል። ቡድኑ በ28 ነጥብ የሊጉ አናት ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው አርባምንጭ ከተማ በሊጉ ምንም ጨዋታ ያለሸነፈ ብቸኛ ቡድን ነው። ስድስት ጊዜ ሲሸነፍ በሰባቱ አቻ ወጥቷል። በጨዋታዎቹ ላይ አምስት ግቦችን ሲያስቆጥር 14 ጎሎችን አስተናግዷል። አርባምንጭ ከተማ በሰባት ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ሲዳማ ቡና ካሸነፈ የሊጉን መሪነት ያጠናክራል። አርባምንጭ ከተማ በሊጉ የመጀመሪያ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። በሌላኛው መርሃ ግብር ምድረገነት ሽሬ ከነጌሌ አርሲ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ምድረገነት ሽሬ እስከ አሁን በሊጉ 13 ጨዋታዎችን አድርጎ አራት ጊዜ ሲያሸንፍ በተመሳሳይ በአራቱ ተሸንፏል። አምስት ጊዜ ነጥብ ጥሏል። 11 ግቦችን ሲያስቆጥር ዘጠኝ ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ17 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል። አዲስ አዳጊው ነጌሌ አርሲ በሊጉ ባከናወናቸው 13 ጨዋታዎች በስድስቱ ሲያሸንፍ በሶስቱ ሽንፈት አስተናግዷል። አራት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 15 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ ዘጠኝ ግቦች ተቆጥረውበታል። ነጌሌ አርሲ በ22 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ምድረገነት ሽሬ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ፣ ነጌሌ አርሲ በድል ጉዞው ለመቀጠል ይጫወታሉ። ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከአዳማ ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ10 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። አዳማ ከተማ በ21 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ጨዋታው ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው።
የማድሪድ ደርቢ በስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ
Jan 8, 2026 78
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 30/2018(ኢዜአ)፦ በስፔን የአሸናፊዎች ዋንጫ አትሌቲኮ ማድሪድ እና ሪያል ማድሪድ ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በኪንግ አብደላ ስፖርትስ ስታዲየም ይካሄዳል። ሁለቱ ክለቦች በስፔን የአሸናፊዎች ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለአምስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም በተደረጉት አራት ጨዋታዎች ሪያል ማድሪድ ሁለት ጊዜ ሲያሸነፍ አትሌቲኮ ማድሪድ በአንዱ ድል ሲቀናው በአንዱ ጨዋታ አቻ ተለያይቷል። ሁለቱ ቡድኖች ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ2024 በግማሽ ፍጻሜ ሲሆን በወቅቱ ሪያል ማድሪድ 5 ለ 3 በማሸነፍ ለፍጻሜ አልፏል። በወቅቱ ሪያል ማድሪድ በፍጻሜው ባርሴሎናን 4 ለ 1 በማሸነፍ ዋንጫ አንስቷል። ከአራቱ ጨዋታዎች አንዱ (እ.አ.አ በ2014) ፍጻሜው በደርሶ መልስ ሲካሄድ የተደረገ ነው። ሪያል ማድሪድ የስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫን 13 ጊዜ ሲያነሳ አትሌቲኮ ማድሪድ ሁለት ጊዜ ውድድሩን አሸንፏል። የሁለቱ ቡድኖች አሸናፊ በፍጻሜው ከባርሴሎና ጋር ይጫወታል። ባርሴሎና ትናንት አትሌቲኮ ቢልባኦን 5 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። የፍጻሜው ጨዋታ እሁድ ጥር 3 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። የስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በስፔን ላሊጋ እና በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ በተመሳሳይ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን የያዙ ክለቦች የሚሳተፉበት ውድድር ነው።
በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ አርሰናል እና ሊቨርፑል የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 8, 2026 100
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት መርሃ ግብር አርሰናል እና ሊቨርፑል ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ይጠበቃል። የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ ከምሽቱ 5 ሰዓት ላይ በኤምሬትስ ስታዲየም ይካሄዳል። አርሰናል በዘንድሮው የውድድር ዓመት ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች 15 ጊዜ ሲያሸንፍ በሁለቱ ተሸንፎ በሶስት አቻ ተለያይቷል። መድፈኞቹ በጨዋታዎቹ 40 ጎሎችን ሲያስቆጥሩ 14 ግቦች ተቆጥረውባቸው በ48 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዘዋል። ተጋጣሚው ሊቨርፑል በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች 10 ጊዜ ሲያሸንፍ ስድስት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዶ በአራቱነጥብ ጥሏል። በጨዋታዎቹ 32 ግቦች ሲያስቆጥሩ 28 ግቦች ተቆጥረውበታል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል በ34 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። አርሰናል እና ሊቨርፑል በሁሉም ውድድሮች እስከ አሁን 245 ጊዜ ተገናኝተዋል። ሊቨርፑል 96 ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ሲይዝ አርሰናል በበኩሉ 83 ጊዜ ሲያሸንፍ 66 ጊዜ አቻ ተለያይተዋል። በፕሪሚየር ሊጉ 67 ጊዜ ተገናኝተው ሊቨርፑል 26 ጊዜ ሲያሸንፍ አርሰናል በ18ቱ ድል ቀንቶታል። በቀሪ 23 ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ባለፉት አምስት የሊግ የእርስ በርስ ጨዋታቸው ሁለቱም በተመሳሳይ አንድ ጊዜ ሲያሸንፉ በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ሁለቱ ቡድኖች በዘንድሮ የሊግ መርሃግብር በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት ጨዋታ ሊቨርፑል 1 ለ 0 ማሸነፉ ይታወሳል። አርሰናል ካሸነፈ ከተከታዩ ማንችስተር ሲቲ ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ ስምንት ከፍ ያደርጋል። የ47 ዓመቱ አንቶኒ ቴይለር የሁለቱን ቡድኖች ተጠባቂ ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል።
ማንችስተር ሲቲ ነጥብ ጣለ
Jan 7, 2026 101
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 29/2018(ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ121ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ማንችስተር ሲቲ እና ብራይተን አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በኢትሃድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አርሊንግ ሃላንድ በ41ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠራት ጎል ማንችስተር ሲቲን መሪ አድርጓል። ሃላንድ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ወደ 20 በማሳደግ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን አጠናክሯል። ካሩ ሚቶማ በ60ኛው ደቂቃ ለብራይተን የአቻነቷን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ማንችስተር ሲቲ ከእረፍት መልስ ጨዋታውን ማሸነፍ የሚችልባቸውን እድሎች መጠቀም አልቻለም። የቡድኑ የተከላካይ ክፍል በጉዳት መሳሳት ለአደጋ ተጋላጭ አድርጓታል። በሊጉ ለሶስት ተከታታይ ጨዋታዎች አቻ የወጣው ማንችስተር ሲቲ በ43 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከአርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማጥበብ እድሉን ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ብራይተን በ29 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። በሌሎች የሊጉ መርሃግብሮች በርንሌይ እና ማንችስተር ዩናይትድ ሁለት አቻ ተለያይተዋል። በተርፍ ሙር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቤንጃሚን ሼስኮ ሁለቱንም ግቦች ለዩናይትድ ከመረብ ላይ አሳርፏል። የዩናይትዱ ተከላካይ አይደን ሄቨን በራሱ ላይ እና ጄይደን አንቶኒ ለበርንሌይ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ማንችስተር ዩናይትድ ከሩበን አሞሪም ስንብት በኋላ በጊዜያዊ አሰልጣኝ ዳረን ፍሌቸር እየተመራ የመጀመሪያ ነጥቡን ሲያገኝ በ32 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ፉልሃም ቼልሲን 2 ለ 1 ሲያሸንፍ ራውል ሂሜኔዝ እና ሃሪ ዊልሰን የማሸነፊያ ግቦቹን ሲያስቆጥሩ ሊያም ዴላፕ ብቸኛውን ጎል ለቼልሲ ከመረብ አሳርፏል። የቼልሲው ማርኮ ኩኮሬያ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል። በስልኸረስት ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ክሪስታል ፓላስ እና አስቶንቪላ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። አስቶንቪላ በ43 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ብሬንትፎርድ ሰንደርላንድን 3 ለ 0 ሲረታ ቦርንማውዝ ቶተንሃም ሆትስፐርስን 3 ለ 2 እና ኒውካስትል ዩናይትድ ሊድስ ዩናይትድን 4 ለ 3 አሸንፈዋል። ኤቨርተን ከዎልቭስ ያደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተጠናቋል።
ባርሴሎና በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ለፍጻሜ አለፈ
Jan 7, 2026 63
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 29/2018(ኢዜአ)፦ በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ የመጀመሪያ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ባርሴሎና አትሌቲኮ ቢልባኦን 5 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል። ማምሻውን በሳዑዲ አረቢያ ኪንግ አብደላ ስፖርትስ ሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ራፊኒያ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ፌርሚን ሎፔዝ፣ ፌራን ቶሬስ እና ሮኒ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ላይ ባርሴሎና ከፍተኛ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። ባርሴሎና በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ለፍጻሜ ያለፈ የመጀመሪያው ክለብ ሆኗል። በፍጻሜው ከአትሌቲኮ ማድሪድ እና ሪያል ማድሪድ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። አትሌቲኮ ማድሪድ እና ሪያል ማድሪድ ነገ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ማንችስተር ሲቲ ከብራይተን ይጫወታል
Jan 7, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 29/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ ስምንት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ ማንችስተር ሲቲ ከብራይተን በኢትሃድ ስታዲየም ጨዋታውን ያደርጋል። ማንችስተር ሲቲ በ42 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ብራይተን በ28 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ነጥብ የጣለው ማንችስተር ሲቲ ማሸነፍ ከአርሰናል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት በጊዜያዊነት ወደ ሶስት ዝቅ ማድረግ ያስችለዋል። ብራይተን ካሸነፈ በሊጉ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። በሌሎች መርሃ ግብሮች በርንሌይ ከማንችስተር ዩናይትድ ምሽት 5 ሰዓት ከ15 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን ያሰናበተው ማንችስተር ዩናይትድ በጊዜያዊ አሰልጣኝ ዳረን ፍሌቸር እየተመራ ወደ ሜዳ ይገባል። በርንሌይ ባለፉት 10 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ክሪስታል ፓላስ ከአስቶንቪላ፣ ፉልሃም ከቼልሲ፣ ብሬንትፎርድ ከሰንደርላንድ፣ ቦርንማውዝ ከቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ኤቨርተን ከዎልቭስ በተመሳሳይ ምሽት 4 ሰዓት ከ30 ላይ ይጫወታሉ። ኒውካስትል ዩናይትድ ከሊድስ ዩናይትድ ምሽት 5 ሰዓት ከ15 ላይ በሴንት ጀምስ ፓርክ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
ባርሴሎና ከአትሌቲኮ ቢልባኦ ለስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ፍጻሜ ለማለፍ ይጫወታሉ
Jan 7, 2026 82
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 29/2018 (ኢዜአ)፦ የስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ የግማሽ የፍጻሜ መርሃ ግብር ዛሬ እና ነገ በሳዑዲ አረቢያ ይካሄዳል። ምሽት አራት ሰዓት ባርሴሎና ከአትሌቲኮ ቢልባኦ ጋር በኪንግ አብደላ ስፖርትስ ሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባርሴሎና 15 ጊዜ ውድድሩን በማሸነፍ የክብረ ወሰኑ ባለቤት ነው። አትሌቲኮ ቢልባኦ ሶስት ጊዜ ዋንጫውን አንስቷል። ሁለቱ ክለቦች በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ ሲገናኙ የአሁኑ ለዘጠነኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም ባደረጓቸው ስምንት ጨዋታዎች ባርሴሎና አራት ጊዜ ሲያሸንፍ አትሌቲኮ ቢልባኦ ሶስት ጊዜ ድል ቀንቶታል። አንድ ጊዜ አቻ ወጥተዋል። ከስምንቱ ጨዋታዎች ስድስቱ የፍጻሜው ጨዋታ ደርሶ መልስ በነበረበት ወቅት የተካሄዱ ናቸው። እ.አ.አ በ2025 በስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በጅዳ ባደረጉት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ባርሴሎና በጋቪ እና ላሚን ያማል ግቦች 2 ለ 0 አሸንፏል። እ.አ.አ በ2021 በፍጻሜው ተገናኝተው አትሌቲኮ ቢልባኦ 3 ለ 2 አሸንፏል። በ2025/26 የስፔን ላሊጋ ባርሴሎና በ49 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። አትሌቲኮ ቢልባኦ በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። የዛሬው ጨዋታ አሸናፊ ክለብ በፍጻሜው ከአትሌቲኮ ማድሪድ እና ሪያል ማድሪድ አሸናፊ ጋር ይጫወታል። የስፔን አሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ የተጀመረው እ.አ.አ 1982 ነው። ውድድሩ እ.አ.አ 1982 እስከ 2019 የስፔን ላሊጋ እና የስፔን የኮፓ ዴል ሬይ (ጥሎ ማለፍ) ዋንጫ አሸናፊዎች የሚጫወቱበት ነበር። የስፔን እግር ኳስ ማህበር እ.አ.አ በ2020 ባደረገው ማስተካከያ የስፔን የአሸናፊዎች አሸናፊ ዋንጫ በስፔን ላሊጋ እና በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ በተመሳሳይ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃን የያዙ ክለቦች እንዲሳተፉ ተደርጓል። ባርሴሎና የወቅቱ የላሊጋ እና የኮፓ ዴል ሬይ አሸናፊ ሲሆን ሪያል ማድሪድ በሁለቱም ውድድሮች ላይ ሁለተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። እንደዚህ አይነት ሁኔታ በሚገጥምበት ወቅት በሊጉ ሶስተኛ እና አራተኛ ደረጃን ይዘው ያጠናቀቁ ክለቦች እንደሚሳተፉ የውድድር ደንቡ ያስቀምጣል። በዚሁ መሰረት አትሌቲኮ ማድሪድ እና አትሌቲኮ ቢልባኦ በዘንድሮው ውድድር ላይ ተሳታፊ ሆነዋል።
የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ለሩብ ፍጻሜ አለፈች
Jan 7, 2026 101
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ኮትዲቯር ቡርኪናፋሶን 3 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በማራካሽ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታው አማድ ዲያሎ በ20ኛው፣ ያን ዲዮማንዴ በ32ኛው እና ባዙማና ቱሬ በ87ኛው ደቂቃ የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አማድ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ግቦች ብዛት ወደ ሶስት ከፍ አድርጓል። ተጫዋቹ ከጎሉ በተጨማሪ ለዲዮማንዴ ጎል ኳሱን አመቻችቶ አቀብሏል። የጨዋታው ኮከብ ሆኖም ተመርጧል። በጨዋታው ላይ ኮትዲቯር ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ድሉን ተከትሎ የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ሩብ ፍጻሜ የገባች የመጨረሻዋ ሀገር ሆናለች። በሩብ ፍጻሜው ከሰባት ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ግብጽ ጋር የምታደረገው ጨዋታ ከወዲሁ የሚጠበቅ ነው። ዛሬ በተደረገ ሌላኛው የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር አልጄሪያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን 1 ለ 0 በማሸነፍ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቅላች። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ተጠናቋል። አዘጋጇ ሞሮኮ ከካሜሮን፣ ኮትዲቯር ከግብጽ ፣ ናይጄሪያ ከአልጄሪያ እና ማሊ ከሴኔጋል በሩብ ፍጻሜው ይጫወታሉ። የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ጥር 1 እና 2 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳሉ።
ኖቲንግሃም ፎረስት ዌስትሃም ዩናይትድን በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አገኘ
Jan 7, 2026 78
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኖቲንግሃም ፎረስት ዌስትሃም ዩናይትድን 2 ለ 1 አሸንፏል። ማምሻውን በለንደን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የኖቲንግሃም ፎረስት ተከላካይ ሙሪሎ በ13ኛው ደቂቃ በራሱ ላይ ያስቆጠረው ጎል ዌስትሃምን መሪ አድርጓል። ኒኮላስ ዶሚኒጌዝ በ55ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፈው ጎል ኖቲንግሃም ፎረስት አቻ ሆኗል። ሞርጋን ጊብስ-ዋይት በ89ኛው በፍጹም ቅጣት ምት ያስቆጠረው ግብ ለፎረስት ወሳኝ ሶስት ነጥብ አስገኝቷል። የዌስትሃም ዩናይትዱ ክሪሴንሲዮ ሳመርቪል በ51ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ግብ በቪዲዮ በታገዘ ዳኝነት (ቫር) ታይቶ ከጨዋታ ውጪ በመሆኑ ምክንያት ሊሻር ችሏል። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኖቲንግሃም ፎረስት በ21 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ስድስተኛ ድሉን አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ዌስትሃም ዩናይትድ በ14 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሌ። ዌስትሃም ዩናይትድ ባለፉት 10 የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ታህሳስ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
አልጄሪያ ሩብ ፍጻሜውን ተቀላቀለች
Jan 6, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ሰባተኛ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር አልጄሪያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን በፕሪንስ ሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ በ90 ደቂቃ ምንም ግብ ባለመቆጠሩ ምክንያት 30 ደቂቃ ተጨምሯል። በተጨማሪ ሰዓት አዲል ቡልቢና በ119ኛው ደቂቃ አልጄሪያን አሸናፊ ያደረገችውን ወሳኝ ግብ አስቆጥሯል። አልጄሪያ ሩብ ፍጻሜ የገባች ሰባተኛ ሀገር ሆናለች። በሩብ ፍጻሜው ከናይጄሪያ ጋር የምትጫወት ይሆናል። የጥሎ ማለፍ የመጨረሻ ጨዋታ በወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር እና ቡርኪናፋሶ መካከል ምሽት አራት ሰዓት ላይ በማራካሽ ስታዲየም ይካሄዳል።
ሊያም ሮሴንየር የቼልሲ አሰልጣኝ ሆነው ተሾሙ
Jan 6, 2026 93
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ ቼልሲ ሊያም ሮሴንየርን የክለቡ ዋና አሰልጣኝኝ አድርጉ ዛሬ በይፋ መሾሙን አስታወቀ። ሮሴንየር ከምዕራብ ለንደኑ ክለብ ጋር እስከ እ.አ.አ 2032 የሚያቆያቸውን ውል ተፈራርመዋል። የ41 ዓመቱ እንግሊዛዊ አሰልጣኝ ላለፉት ሁለት ዓመታት በፈረንሳዩ ስትራስቡርግ ክለብ ሲያሰለጥኑ ቆይተዋል። ቼልሲ ባለፈው ሳምንት ጣልያናዊውን አሰልጣኝ ኤንዞ ማሬስካን ማሰናበቱ የሚታወስ ነው።
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ዛሬ ይጀመራል
Jan 6, 2026 118
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛሬ በዌስትሃም ዩናይትድ እና ኖቲንግሃም ፎረስት መካከል ዛሬ ይደረጋል። ጨዋታው ምሽት አምስት ላይ በለንደን ስታዲየም ይካሄዳል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ14 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ኖቲንግሃም ፎረስት በ17 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዟል። የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ከቡርኪናፋሶ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው ባለሜዳው ዌስትሃም ዩናይትድ ባለፉት ዘጠኝ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ተጋጣሚው ኖቲንግሃም ፎረስት በበኩሉ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ሽንፈት አስተናግዷል። ዌስትሃም ዩናይትድ እና ኖቲንግሃም ፎረስት ወሳኝ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይፋለማሉ። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያው ዙር እርስ በእርስ ባደረጉት ጨዋታ ዌስትሃም ዩናይትድ 3 ለ 0 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ቶኒ ሃሪንግተን ጨዋታውን በዋና ዳኝነት ጨዋታውን ይመሩታል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት መርሃ ግብር እስከ ታህሳስ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ከቡርኪናፋሶ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው
Jan 6, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 28/2018 (ኢዜአ)፦በአፍሪካ ዋንጫ ወደ ሩብ ፍጻሜ የሚያልፉ ቀሪ ሁለት ሀገራት የሚለዩባቸው ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። የወቅቱ የዋንጫ ባለቤት ኮትዲቯር ከቡርኪናፋሶ ጋር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በማራካሽ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኮትዲቯር በምድብ ስድስት በሰባት ነጥብ አንደኛ በመያዝ 16 ውስጥ ገብታለች። ተጋጣሚዋ ቡርኪናፋሶ በምድብ አምስት በስድስት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፍ መግባቷን አረጋግጣለች። ግብጽ ለሩብ ፍጻሜ አለፈች ናይጄሪያ ለሩብ ፍጻሜ አለፈች ሁለቱ ጎረቤት ሀገራት በአፍሪካ ዋንጫው ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። አንጎላ እ.አ.አ በ2010 ባዘጋጀችው 27ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሁለት ተገናኝተው ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን እ.አ.አ በ2012 በጣምራ ባዘጋጁት 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በተመሳሳይ በምድብ ሁለት ባደረጉት ጨዋታ ኮትዲቯር 2 ለ 0 አሸንፋለች። ሰለሞን ካሉ እና የቡርኪናፋሶው የቀድሞ ተጫዋች ባካሪ ኮኔ በራሱ ላይ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ኮትዲቯር የሁለት ጊዜ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ናት። ቡርኪናፋሶ ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ2013 ባዘጋጀችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለፍጻሜ ደርሳ በናይጄሪያ 1 ለ 0 የተሸፈችበት ውጤት በአህጉራዊ መድረኩ ምርጡ ውጤቷ ነው። ኮትዲቯር የአፍሪካ ዋንጫ ክብሯን የማስጠበቅ ጉዞዋ ለመቀጠል ከቡርኪናፋሶ ጠንካራ ፈተና ይጠብቃታል። የጨዋታው አሸናፊ ሀገር በሩብ ፍጻሜው ከግብጽ ጋር ይጫወታል። በሌላኛው የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ምሽት አንድ ሰዓት ላይ አልጄሪያ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በሙላይ ኤል ሀሰን ስታዲየም ይጫወታሉ። አልጄሪያ በምድብ አምስት በዘጠኝ ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዛ በማጠናቅ ጥሎ ማለፍ ገብታለች። ተጋጣሚዋ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ በምድብ አራት በሰባት ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅላለች። ሀገራቱ ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ዋንጫ ሁለት ጊዜ ተገናኝተዋል። ሞሮኮ እ.አ.አ በ1998 ባዘጋጀችው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ አንድ ተገናኝተው አልጄሪያ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎን (በወቅቱ አጠራሯ ዛየር) 1 ለ 0 አሸንፋለች። አብዱልቃድር ፌርሃዊ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። እ.አ.አ በ2000 በጋና በተካሄደው 22ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በምድብ ሁለት ተገናኝተው ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ከ25 ዓመታት በኋላ በጥሎ ማለፍ የተገናኙት ሁለቱ ሀገራት ወደ ሩብ ፍጻሜ ለማለፍ ጠንካራ ፍልሚያ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። የቡድኖቹ ጨዋታ አሸናፊ ከናይጄሪያ ጋር በሩብ ፍጻሜው ይገናኛል። አዘጋጇ ሞሮኮ፣ ናይጄሪያ፣ ሴኔጋል፣ ካሜሮን፣ ግብጽ እና ማሊ እስከ አሁን ሩብ ፍጻሜ የገቡ ሀገራት ናቸው።
ናይጄሪያ ለሩብ ፍጻሜ አለፈች
Jan 5, 2026 202
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ናይጄሪያ ሞዛምቢክን 4 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፋለች። ማምሻውን በፌዝ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ቪክቶር ኦሲሜን ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አዴሞላ ሉክማን እና አኮር አዳምስ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። በጨዋታው ላይ ናይጄሪያ ከፍተኛ ብልጫ የወሰደች ሲሆን ተመጣጣኝ ፉክክር ለማየት አልታቸለም። የናይጄሪያው የክንፍ መስመር ተጫዋች አዴሞላ ሉክማን የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ ናይጄሪያ ሩብ ፍጻሜውን የተቀላቀለች ስድስተኛ ሀገር ሆናለች። በሩብ ፍጻሜው ከአልጄሪያ እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች።
ግብጽ ለሩብ ፍጻሜ አለፈች
Jan 5, 2026 168
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አምስተኛ የጥሎ ማለፍ መርሃ ግብር ግብጽ ቤኒንን 3 ለ 1 አሸንፋለች። ማምሻውን በአጋዲር ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ መሐመድ አቴያ በ69ኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ግብ ግብጽን መሪ አድርጋለች። ጆዴል ዶሱ በ83ኛው ደቂቃ የቤኒን የአቻነት ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት በመጠናቀቁ ወደ ተጨማሪ ሰዓት አምርቷል። በጭማሪው ሰዓት ያስር ኢብራሂም በ97ኛው እና መሐመድ ሳላህ በ124ኛው ደቂቃ ያስቆጠሯቸው ጎሎች ግብጽን አሸናፊ አድርጓል። ቡድኖቹ በጨዋታው ላይ ጠንካራ ፉክክር አድርገዋል። ውጤቱን ተከትሎ ሩብ ፍጻሜ የገባች አምስተኛ ሀገር ትሆናለች። በሩብ ፍጻሜው ከኮትዲቯር እና ቡርኪናፋሶ ትጫወታለች።
መቀሌ 70 እንደርታ በሊጉ ሁለተኛ ድሉን አስመዘገበ
Jan 5, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ ኢትዮጵያ መድንን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፍጹም ዓለሙ በ25ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ ሁለተኛ ድሉን ያስመዘገበው መቀሌ 70 እንደርታ በ11 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በአንጻሩ በሊጉ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮጵያ መድን በ13 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ዛሬ በተደረገ ሌላኛው ጨዋታ ባህር ዳር ከተማ እና ድሬዳዋ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ13ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ተጠናቋል። የ14ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከታህሳስ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ እንደሚካሄዱ የሊጉ አክሲዮን ማህበር አስታውቋል።