ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ 70 እንደርታ ለኢትዮጵያ ዋንጫ ፍጻሜ ለማለፍ ይጫወታሉ
May 25, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ዋንጫ የመጀመሪያ የግማሽ ፍፃሜ መርሐ ግብር ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ 70 እንደርታ ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታው ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት በአዲስ አበባ ስታዲየም ይካሄዳል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በሩብ ፍጻሜው መቻልን በመለያ ምት በማሸነፍ አራት ውስጥ ገብቷል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ በበኩሉ በሩብ ፍጻሜው ቦዲቲ ከተማን 3 ለ 2 በማሸነፍ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል። ሁለቱ ቡድኖች በዘንድሮው የውድድር ዓመት ለሶስተኛ ጊዜ ይገናኛሉ። በዘንድሮው የውድድር ዓመት በሊጉ ሁለት ጊዜ ተገናኝተው በተመሳሳይ አንድ አንድ ጊዜ አሸንፈዋል። ሁለቱ ቡድኖች በሊጉ የ27ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ተገናኝተው መቀሌ 70 እንደርታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲን 2 ለ 1 ማሸነፉ የሚታወስ ነው። ፍፁም አለሙ እና ኮትዲቯራዊው አብዱላጢፍ ባምባ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ዳዊት ገብሩ ለወልዋሎ ግቧን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በፕሪሚየር ሊጉ በ40 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ በ34 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። የጨዋታው አሸናፊ ቡድን በፍጻሜው ከሲዳማ ቡና እና ኢትዮጵያ መድን አሸናፊ ጋር ይጫወታል።
የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የመጨረሻ ቀን ውሎ
May 24, 2026 480
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፦ የ2025/26 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ማምሻውን ተጠናቋል። ሁሉም የ38ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በተመሳሳይ ሰዓት ተደርገዋል:: የሻምፒዮኖቹ አርሰናል የድል ፌሽታ ሲያነሳ፣ የጎረቤቱ ቶተንሃም ከመውረድ መትረፍ፣ የዌስትሃም ከሊጉ መሰናበት፣ የሊቨርፑል የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ማረጋገጥ እና የብሩኖ ፈርናንዴዝ አዲስ ክብረ ወሰን፤ እለቱን በክስተቶች የታጀበ አድርጎታል። በሳምንቱ አጋማሽ ከ22 ዓመታት የሊጉ ሻምፒዮን መሆኑን ያረጋገጠው አርሰናል ለረጅም ጊዜ የናፈቀውን ዋንጫ በደማቅ ስነ ስርዓት አንስቷል። መድፈኞቹ በሰልኸረስት ፓርክ ባደረጉት ጨዋታ ክሪስታል ፓላስን 2 ለ 1 አሸንፈዋል። ጋብርኤል ጄሱስ እና ኖኒ ማዱዌኬ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ጂን ፍሊፕ ማቴታ የፓላስን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። አርሰናል በ85 ነጥብ ዓመቱን በአንደኝነት ተጠናቋል። ከጨዋታው በፊት የክሪስታል ፓላስ ተጫዋቾች በግራ እና በቀኝ በመቆም ለሻምፒዮኑ አርሰናል የክብር አቀባበል (Guard of honour) አድርገዋል። ተከታዩ ማንችስተር ሲቲ በአስቶንቪላ የ2 ለ 1 ሽንፈት አስተናግዷል። ኦሊ ዋትኪንስ ለቪላ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥሯል። አንቶዋን ሴሜኒዮ የሲቲን ጎል ከመረብ አገናኝቷል። ሲቲ በ78 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። የውሃ ሰማያዊዎቹ አሰልጣኝ ፔፔ ጋርዲዮላ ከጨዋታው በኋላ ክለቡን በይፋ ተሰናብቷል። በርናንዶ ሲልቫም ሲቲን ተሰናብቷል። የማንችስተር ሲቲው አርሊንግ ሃላንድ በ27 ጎሎች የሊጉ ኮከብ ግብ አስቆጣሪ በመሆን ተጠናቋል። በሊጉ የመዝጊያ ቀን ሲጠበቁ ከነበሩ ጉዳዮች መካከል አንዱ ላለመውረድ የሚደረግ ትግል ነው። ቶተንሃም ሆትስፐርስ በሜዳው ኤቨርተንን አስተናግዶ 1 ለ 0 በማሸነፍ በ41 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ በሊጉ መቆየቱን አረጋግጧል። ጆአኦ ፓሊኒያ የስፐርስን ብቸኛ ጎል አስቆጥሯል። ዌስትሃም ዩናይትድ ሊድስ ዩናይትድን 3 ለ 0 ቢያሸንፍም ከሊጉ ወርዷል። ቫለንቲን ካስቴላኖስ፣ጃሬድ ቦወን እና ካሉም ዊልሰን ግቦቹን አስቆጥረዋል። ዌስትሃም ዩናይትድ በ39 ነጥብ 18ኛ ደረጃን በመያዝ ከሊጉ ተሰናብቷል። የለንደኑ ክለብ ከ14 ዓመታት የሊጉ ቆይታ በኋላ ወደ ሻምፒዮንሺፑ ወርዷል። ሊቨርፑል ከብሬንትፎርድ አንድ አቻ በመለያየት በ60 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን አረጋግጧል። መሐመድ ሳላህ እና አንዲ ሮበርትሰን ከጨዋታው በኋላ ሊቨርፑልን በይፋ ተሰናብተዋል። ሰንደርላንድ ቼልሲን 2 ለ 1 በመርታት በ54 ነጥብ የዩሮፓ ሊግ ተሳታፊነት ትኬቱን ቆርጧል። ቦርንማውዝ ሌላኛው የዩሮፓ ተሳታፊ ክለብ ነው። ቡዱኑ ዛሬ ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር አንድ አቻ በመለያየት በ57 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። ቼልሲ በ52 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዞ በመጨረስ ከአውሮፓ መድረክ ተሳትፎ ውጪ ሆኗል። ማንችስተር ዩናይትድ ብራይተንን 3 ለ 0 አሸንፏል። በአሜክስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፓትሪክ ዶርጉ፣ ብሪያን ምቡዌሞ እና ብሩኖ ፈርናንዴዝ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ለዶርጉ ጎል መቆጠር እጁ የነበረበት ብሩኖ ፈርናንዴዝ በዓመቱ 21 ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል አዲስ ክብረ ወሰን አስመዝግቧል። ከዚህ ቀደም ቲዬሪ ሄነሪ እና ኬቨን ደ ብሮይን (በተመሳሳይ 20 ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል) በጣምራ ይዘው የነበሩትን ክብረ ወሰን አሻሽሏል። ፈርናንዴዝ ትናንት የሊጉ የዓመቱ ምርጣ ተጫዋች በመባል መመረጡ አይዘነጋም። ዩናይትድ በ71 ነጥብ ሶስተኛ ሆኖ ዓመቱን አጠናቋል። ብራይተን በ53 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ በኮንፍረንስ ሊግ መሳተፉን አረጋግጧል። ፋልሃም ኒውካስትል ዩናይትድን 2 ለ 0 ሲያሸንፍ ወራጆቹ በርንሌይ እና ዎልቭስ ባደረጉት ጨዋታ አንድ አቻ ተለያይተዋል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ እስከ መጨረሻው ደቂቃ በድራማ እና ትዕይንቶች ታጅቦ ተጠናቋል።
የኢትዮጵያ ከ 17 ዓመት በታች ሴት ብሔራዊ ቡድን የቡሩንዲ አቻውን 2ለ1 አሸንፏል
May 24, 2026 331
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ 17ዓመት በታች ሴት ብሔራዊ ቡድን ከቡሩንዲ ያደረገውን የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ሁለተኛ ዙር የመጀመሪያ ጨዋታ 2ለ1 አሸንፏል። አበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ለቡድኑ የማሸነፊያ ሁለት ግቦችን ሊዲያ እያሱ ማስቆጠር ችላለች። ኢትዮጵያ በ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ደቡብ ሱዳንን በድምር ውጤት 8 ለ 0 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፉ ይታወቃል። ተጋጣሚዋ ብሩንዲ በመጀመሪያው ዙር ማላዊን በአጠቃላይ ውጤት 4 ለ 2 አሸፋለች። የሁለቱ ቡድኖች የመልስ ጨዋታው ግንቦት 23 ቀን 2018 ዓ.ም ቡጁምቡራ ላይ ይካሄዳል። ኢትዮጵያ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈች ለመጨረሻው ዙር ማጣሪያ ትጫወታለች። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን የማጣሪያ ጨዋታውን ከብሩንዲ ጋር ያከናውናል
May 24, 2026 306
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፦ በ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ ኢትዮጵያ ከብሩንዲ ጋር ዛሬ የመጀመሪያ ጨዋታዋን ታደርጋለች። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይካሄዳል። ኢትዮጵያ በ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ደቡብ ሱዳንን በድምር ውጤት 8 ለ 0 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር ማለፉ ይታወቃል። ተጋጣሚዋ ብሩንዲ በመጀመሪያው ዙር ማላዊን በአጠቃላይ ውጤት 4 ለ 2 አሸፋለች። አሰልጣኝ ራውዳ አሊ ለማጣሪያ ጨዋታው ግንቦት 5 ቀን 2018 ዓ.ም ለ30 ተጫዋቾች ጥሪ ካደረጉበት ጊዜ አንስቶ ብሔራዊ ቡድኑ ልምምዱን ሲያደርግ ቆይቷል። ራውዳ የመጀመሪያ ጥሪ ከተደረገላቸው 30 ተጫዋቾችች መካከል አምስቱን በመቀነስ ቡድኑ ዝግጅቱን ቀጥሏል። ብሔራዊ ቡድኑ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት በአበበ በቂላ ስታዲየም ማድረጉንና ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በፓትሪክ ሳንጋዋ የሚመራው የብሩንዲ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከኢትዮጵያ ጋር ለሚያደርገው ጨዋታ ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቷል። የሁለቱ ቡድኖች የመልስ ጨዋታው ግንቦት 23 ቀን 2018 ዓ.ም ቡጁምቡራ ላይ ይካሄዳል። ኢትዮጵያ በደርሶ መልስ ውጤት ካሸነፈች ለመጨረሻው ዙር ማጣሪያ ትጫወታለች። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። በማጣሪያ የሚያልፉ አራት የአፍሪካ ሀገራት በሶስት ዙሮች በሚደረጉ ጨዋታዎች ይለያሉ።
አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት እናደርጋታለን ብለን ስንነሳ በአካልና በአዕምሮ የዳበረ ትውልድ መገንባትን ቅድሚያ በመስጠት ነው-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 24, 2026 330
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 16 /2018 (ኢዜአ)፦ አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት እናደርጋታለን ብለን ስንነሳ በአካልና በአዕምሮ የዳበረ ትውልድ መገንባትን ቅድሚያ በመስጠት ነው ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለፁ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በቦሌ ክፍለ ከተማ 5 ስፖርት ማዘውተሪያዎችን፣ 95 የህጻናት መጫዎቻዎችን፣ 6 የህጻናት ማቆያዎችን (day cars )፣ ካፍቴሪያዎችን፣ አንፊ ትያትሮችን እንዲሁም በርካታ የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚሰጡ መሰረተ ልማቶችን ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። በተለይ ካፒቴን አበራ ለሚ ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ የገነቡት በ4,900 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያረፈው ስታዲየም የእግር ኳስ መጫወቻ ሜዳ፣ የመሮጫ ትራክ፣ ጥላ ያለው የተመልካች መቀመጫ፣ ለወጣቶች የስራ እድል የሚውሉ ሱቆች፣ መታጠቢያና መጸዳጃ ቤቶች፣ ጂምናዚየም እና የእቃ ማከማቻ መጋዘንን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። የለሚ ኮሚኒቲ ስታዲየምን ገንብተው ያስረከቡትን ካፒቴን አበራ ለሚን በራሴና በከተማ አስተዳደሩ ስም አመሰግናለሁ ያሉት ከንቲባዋ የአካባቢው ነዋሪዎችም ስታዲየሙን በእንክብካቤ እንዲጠቀሙበት አሳስበዋል። ከንቲባ አዳነች በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፥ የክፍለ ከተማዉ አመራሮችንም ለሰራችሁት ድንቅ ስራ ምስጋና ይገባችኋል ብለዋል።
ባየር ሙኒክ የጀርመን ጥሎ ማለፍ ዋንጫን አነሳ
May 24, 2026 211
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፦ በጀርመን የጥሎ ማለፍ ዋንጫ (DFB-Pokal) ባየር ሙኒክ ስቱትጋርትን 3 ለ 0 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በበርሊን በሚገኘው የኦሊምፒክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሃሪ ኬን ሁለት በጨዋታ እና አንድ በፍጹም ቅጣት ግቦች በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ኬን በዘንድሮው የውድድር ዓመት ያስቆጠራቸውን አጠቃላይ ጎሎች 61 አድርሷል። ባየር ሙኒክ በተጋጣሚው ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። ውጤቱን ተከትሎ ባየር ሙኒክ ለ21ኛ ጊዜ የጥሎ ማለፉን ዋንጫ አንስቷል። ሙኒክ ከጀርመን ቡንድስሊጋ እና የፍራንዝ ቤከንባወር የአሸናፊዎች አሸናፊ ውድድር በኋላ ሶስተኛ ዋንጫውን አንስቷል። የባለፈው ዓመት የውድድሩ አሸናፊ የነበረው ስቱትጋርት የዋንጫ ክብሩን ማስጠበቅ አልቻለም። ቡድኑ የውድድሩ የአራት ጊዜ አሸናፊ ነው። የጀርመን ጥሎ ማለፍ 91 ዓመታትን ያስቆጠረ ውድድር ነው።
አርሰናል የዋንጫ አቀባበል፣ የአውሮፓ ተሳትፎ ፉክክር፣ የጋርዲዮላ ስንብት እና የቶተንሃምና ዌስትሃም በሊጉ የመቆየት ህልም፦ በሊጉ መዝጊያ ቀን የሚጠበቁ ክስተቶች
May 24, 2026 388
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 16 /2018 (ኢዜአ)፦ ነሐሴ 9 ቀን 2017 ዓ.ም የጀመረው የ2025/26 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ38ኛ ሳምንት ማጠቃለያ ጨዋታዎች ዛሬ በተመሳሳይ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ ፍጻሜያቸውን ያገኛሉ። ከ22 ዓመታት ጥበቃ በኋላ በሳምንቱ አጋማሽ የሊጉን ዋንጫ ማንሳቱን ያረጋገጠው አርሰናል (1ኛ፣ 82 ነጥብ) ወደ ሰልኸረስት ፓርክ በማቅናት ከክሪስታል ፓላስ (15ኛ t፣ 45 ነጥብ) ጋር ይጫወታል። ደጋፊዎቹ መድፈኞቹ ከጨዋታው በኋላ የሚያደርጉትን ይፋዊ የዋንጫ ርክክብ በጉጉት ይጠብቁታል። ከጨዋታው መጀመር በፊት የክሪስታል ፓላስ ተጫዋቾች በግራ እና በቀኝ በመቆም አርሰናል ወደ ሜዳ ሲገባ የክብር አቀባበል (Guard of honour) ያደርጋሉ። የዛሬው ተቀናቃኛቸው ክሪስታል ፓላስ ይህንን ጨዋታ የሚያደርገው ከስፔኑ ራዮ ቫዮካኖ ጋር ለሚያደርገው የአውሮፓ ኮንፈረንስ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ ዋዜማ ላይ ሆኖ ነው። በሌላ በኩል በሳምንቱ አጋማሽ ከቦርንማውዝ ጋር አንድ አቻ ተለያይቶ የዋንጫ ጉዞው ያበቃው ማንችስተር ሲቲ (2ኛ፣ 78 ነጥብ) ዓመቱን በድል ለመዝጋት ከአስቶንቪላ (4ኛ፣ 62 ነጥብ) ጋር በኢትሃድ ስታዲየም ይጫወታል። በሳምንቱ አጋማሽ ከክለቡ መለያየቱ ይፋ የሆነው ፔፕ ጋርዲዮላ የመጨረሻ ጨዋታውን ዛሬ ያደርጋል። አስቶንቪላ በበኩሉ ከዩሮፓ ሊግ ዋንጫ የድል ፌሽታ ማግስት ዓመቱን በአሸናፊነት ለማጠናቀቅ ይፋለማል። በመዝጊያው ቀን ትልቁን ትኩረት የሳበው ሌላው ክስተት በለንደኖቹ ቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ዌስትሃም ዩናይትድ መካከል የሚደረገው የህልውና ፉክክር ነው። ቶተንሃም ከኤቨርተን፣ ዌስትሃም ደግሞ ከሊድስ ዩናይትድ ጋር ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በአሁኑ ሰዓት ስፐርስ በ38 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ሲገኝ፣ ዌስትሃም በ36 ነጥብ 18ኛ ደረጃ ላይ የወራጅ ቀጠናው ውስጥ ይገኛል። የሰሜን ለንደኑ ቶተንሃም በዛሬው ጨዋታ በትንሹ አንድ ነጥብ (አቻ) ካገኘ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል፤ በአንጻሩ ቶተንሃም ተሸንፎ ዌስትሃም ማሸነፍ ከቻለ ግን የዲዘርቢው ስፐርስ ወደ ታችኛው ሊግ መውረዱ ሲረጋገጥ ዌስትሃም በፕሪሚየር ሊጉ ይቆያል። ከወራጅ ቀጠናው ውጪ ወደ አውሮፓ መድረክ (ሻምፒዮንስ ሊግ፣ ዩሮፓ ሊግ እና ኮንፍረንስ ሊግ) ለማለፍ የሚደረገው ፍልሚያ እጅግ ተቀራራቢ ሆኗል። አምስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ሊቨርፑል (59 ነጥብ) ከብሬንትፎርድ (9ኛ፣ 52 ነጥብ) ጋር የሚያደርገውን ጨዋታ ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን ያረጋግጣል። ባለፉት 17 ጨዋታዎች ያልተሸነፈውና የዩሮፓ ሊግ ተሳትፎውን ቀድሞ ያረጋገጠው ቦርንማውዝ (6ኛ፣ 56 ነጥብ) ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር የሚጫወት ሲሆን፤ በሻምፒዮንስ ሊግ ለመሳተፍ አስቶንቪላ 5ኛ ሆኖ ማጠናቀቅ (ቪላ የዩሮፓ ሊግ አሸናፊ በመሆኑ ሊጉን 5ኛ ካጠናቀቀ 6ኛ ደረጃ ላይ ያለውን ክለብ 6ኛ የሻምፒዮንስ ሊግ ኮታ ያደርገዋል። የቦርንማውዝ ሌላኛው ተስፋ የሊቨርፑል መሸነፍ እናኖቲንግሃም ፎረስትን በ6 እና ከዚያ በላይ የጎል ልዩነት ማሸነፍ ነው። በተመሳሳይ ሰባት፣ ስምንት እና አስረኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡት ብራይተን (53 ነጥብ)፣ ቼልሲ (52 ነጥብ) እና ሰንደርላንድ (51 ነጥብ) እርስ በእርስ የሚሻሙ ሲሆን ብራይተን ከማንችስተር ዩናይትድ ጋር በሚያደርገው ጨዋታ ነጥብ የሚጥል ከሆነ ሰንደርላንድን የሚገጥመው ቼልሲ ወይም ብሬንትፎርድ ሰባተኛ ደረጃን በመንጠቅ የአውሮፓ መድረክ ዕድል ያገኛሉ። በሌሎች ጨዋታዎች ቀድመው ከሊጉ መውረደቸውን ያረጋገጡት በርንሌይ እና ዎልቭስ እርስ በእርስ ሲገናኙ፣ ፉልሃም ደግሞ ከኒውካስትል ዩናይትድ ጋር ይጫወታሉ። በአጠቃላይ የሊጉ መዝጊያ ቀን የአርሰናልን የደመቀ የዋንጫ አነሳስ፣ የለንደኖቹን የሞት ሽረት ያለመውረድ ፉክክር እና እስከ መጨረሻዋ ሰከንድ የሚዘልቀውን የአውሮፓ መድረክ ትንቅንቅ በአንድ ላይ አጣምሮ በክብር፣ በደስታ፣ በለቅሶ እና በጸጸት የታጀበ ታሪካዊ ፍጻሜ ያገኛል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ማለፍ አልቻለም
May 23, 2026 417
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ ከ17 ዓመት በታች ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ በተደረገ የመለያ ጨዋታ ሞዛምቢክ ኢትዮጵያን በመለያ ምት አሸንፋለች። በመሐመድ ስድስተኛ ስፖርት ኮምፕሌክስ በተካሄደው ጨዋታ አሚር ሚስባህ በ16ኛው ደቂቃ ያስቆጠረው ጎል ኢትዮጵያን መሪ አድርጓል። ዲዬጎ ፔሌምቤ በ57ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፋት ጎል ሞዛምቢክ አቻ ሆናለች። ጨዋታው በመደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት በመጠናቀቁ ወደ መለያ ምት አምርቷል። በመለያ ምቱም ሞዛምቢክ 5 ለ 4 በማሸነፍ በኳታር አስተናጋጅነት ለሚከናወነው 21ኛው ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ማለፏን አረጋግጣለች። እንየው ስለሺ ከኢትዮጵያ በኩል ፍጹም ቅጣት ምቱን የሳተ ተጫዋች ነው። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ማለፍ አልቻለም። በሌላኛው የመለያ መርሐ ግብር ጋና ከዩጋንዳ ምሽት አራት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዘጋጇ ሞሮኮ፣ ግብጽ፣ ኮትዲቯር፣ ካሜሮን፣ ታንዛንያ፣ ማሊ፣ ሴኔጋል እና አልጄሪያ በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ ሀገራት ናቸው። 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ እስከ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በአፍሪካ ዋንጫው እየተሳተፉ ካሉ 16 ሀገራት መካከል 10ሩ በጥቅምት እና ህዳር ወር 2019 ዓ.ም በኳታር ለሚካሄደው 20ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ተሳታፊ ይሆናሉ። በዓለም ዋንጫው ላይ 48 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ሁል ሲቲ ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ ወደ ፕሪሚየር ሊጉ ተመለሰ
May 23, 2026 312
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ሻምፒዮምሺፕ የጥሎ ማለፍ የፍጻሜ ጨዋታ ሁል ሲቲ ሚድልስቦሮውን 1 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በዌምብሌይ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኦሊ ማክበርኒ በ94ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ሚድልስቦሮው ብልጫ ቢውስድም ሁል ሲቲ በባከነ ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ግብ አሸናፊ አድርጎታል። ውጤቱን ተከትሎ ሁል ሲቲ ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ ወደ እንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መመለሱን አረጋግጧል። ክለቡ ለመጨረሻ ጊዜ በሊጉ ላይ የተወዳደረው እ.አ.አ 2016/17 ነበር። ሚድልስቦሮው ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ ወደ ሊጉ የመመለስ ህልሙ ሳይሳካ ቀርቷል። ኮቨንተሪ ሲቲ እና ኢፕስዊች ታውን አስቀድመው ወደ ፕሪሚየር ሊጉ ማደጋቸውን ያረጋገጡ ክለቦች ናቸው።
በድሬዳዋ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው
May 23, 2026 195
ድሬዳዋ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦በድሬዳዋ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ መሆናቸውን የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ ገለጹ። በብልፅግና ፓርቲ የድሬዳዋ ቅርንጫፍ የምረጡኝ ቅስቀሳ አካል የሆነ አመራሮች፣ የአባላትና ደጋፊዎች የተሳተፉበት የ5 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ተካሂዷል። በመርሐግብሩ ላይ የተሳተፉት የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ሀርቢ ቡህ እንደገለጹት፤ ስፖርት ጤናማ፣ ተወዳዳሪ እና አሸናፊ ትውልድ ለማፍራት መሠረታዊ ጉዳይ በመሆኑ፤ በአስተዳደሩ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች በጥራትና በፍትሐዊነት በገጠርና በከተማ እንዲገነቡ ተደርጓል። ወጣቶች የነገ ብሩህ ሕይወታቸው ፍሬያማ እንዲሆን በየወረዳው የወጣቶች ማዕከላት ተገንብተው አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉንም ገልጸዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በአስተዳደሩ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በብልጽግና ፓርቲ ድሬዳዋ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ በበኩላቸው፤ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ፓርቲው የሕዝብን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ውጤታማ ፕሮጀክቶችን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በድሬዳዋ ገጠርና ከተማ ውጤታማ እና ጤናማ ትውልድ ለማፍራት ለስፖርት ዘርፍ በተሰጠው ትኩረት፣ ተወዳዳሪ ትውልድ በመፍጠር ረገድ ወደር የሌለው ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል። በአስተዳደሩ እየተመዘገቡ የሚገኙ ውጤቶችም ሆኑ እንደ ሀገር እየተከናወኑ የሚገኙ አሻጋሪ ፕሮጀክቶች፣ የኢትዮጵያን ከፍታ ለማረጋገጥ የተጀመረውን ጉዞ ዕውን የሚያደርጉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
ብሩኖ ፈርናንዴዝ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ተብሎ ተመረጠ
May 23, 2026 226
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የማንቸስተር ዩናይትድ አምበል ብሩኖ ፈርናንዴዝ የ2025/26 የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች (Player of the Season) በመሆን መመረጡን የሊጉ አስተዳደር ይፋ አደረገ። የፕሪሚየር ሊጉ አስተዳደር እንደገለጸው፣ የ31 ዓመቱ የመሐል ሜዳ ተጫዋች የዓመቱ ምርጥ ተብሎ የተመረጠው በውድድር ዓመቱ ባሳየው የጎል ዕድሎችን የመፍጠር ብቃትና ለቡድኑ ስኬት ላበረከተው አስተዋጽኦ ነው። ማንቸስተር ዩናይትድ በውድድር ዘመኑ አጋማሽ ላይ በነበረበት የአሰልጣኝ ቅያሬና መዋዠቅ ውስጥ አልፎ በጊዜያዊና በቋሚ አሰልጣኝ ማይክል ካሪክ መሪነት በደረጃ ሰንጠረዡ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ እንዲያጠናቅቅ እንዲሁም ወደ አውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ እንዲመለስ ተጫዋቹ የነበረው ሚና የጎላ እንደነበር ተመላክቷል። ፖርቱጋላዊው አማካይ በውድድር ዓመቱ ስምንት ጎሎችን ማስቆጠር የቻለ ሲሆን፥ በተጨማሪም 20 ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን ለቡድን አጋሮቹ በማቀበል የሊጉን ክብረ ወሰን መጋራት ችሏል። ከዚህ ቀደም ቲዬሪ ሄነሪ (በአርሰናል) እና ኬቨን ደ ብሮይን (በማንችስተር ሲቲ) በነበሩበት ወቅት በተመሳሳይ 20 ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አቀብሏል። ፓርቹጋላዊው አማካይ ቡድኑ ነገ ከብራይተን ጋር በሚያደርገው የመጨረሻ ጨዋታ ላይ ክብረ ወሰኑን ብቻውን የመያዝ ዕድል አለው። በተጨማሪም ብሩኖ ፈርናንዴዝ በዘንድሮው የውድድር ዓመት 132 የግብ ዕድሎችን በመፍጠር የበላይነቱን የያዘ ሲሆን፥ በዚህ ረገድ የሊቨርፑሉ ዶሚኒክ ሶቦስላይ በ89 የጎል ዕድሎች ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ማንቸስተር ዩናይትድ ይህንን የፕሪሚየር ሊግ የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ክብር ሲያገኝ ከ15 ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲሆን፥ የመጨረሻው ሽልማት የተመዘገበው እ.አ.አ በ2010/11 የውድድር ዘመን በሰርቢያዊው ተከላካይ ኔማንያ ቪዲች አማካኝነት እንደነበር ይታወሳል። ፈርናንዴዝ ይህንን ሽልማት ያሸነፈው ከእግር ኳስ ባለሙያዎች፣ ከሊጉ አምበሎችና ከደጋፊዎች በተሰበሰበ ድምፅ ሲሆን፤ ሽልማቱን ለማግኘት ከቀረቡት መካከል ዘንድሮ የሊጉን ዋንጫ ያነሱት የአርሰናል ተጫዋቾች ዴክላን ራይስ፣ ጋብርኤል ማጋሌሽ፣ ዴቪድ ራያ እንዲሁም የማንቸስተር ሲቲውን አርሊንግ ሃላንድ እና አንቶዋን ሴሜኒዮ፣ የኖቲንግሃም ፎረስቱን ሞርጋን ጊብስ-ዋይት እና የሬንትፎርዱን ኢጎር ቲያጎ በብልጫ ማሸነፍ ችሏል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ተጫዋቹ ከቀናት በፊት በፈረንሳይና በእንግሊዝ የእግር ኳስ ጸሐፊዎች ማኅበር (FWA) የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ተብሎ መመረጡ የሚታወስ ሲሆን፥ የክለቡም የዓመቱ ምርጥ ተጫዋች ሽልማትን አግኝቷል። በተያያዘም የማንቸስተር ሲቲው የ21 ዓመት አማካይ ኒኮ ኦራይሊ የሊጉ የዓመቱ ምርጥ ወጣት ተጫዋች በመባል ተመርጧል።
የዓለም ዋንጫ ተሳትፎ ትኬትን ለመቁረጥ 90 ደቂቃዎች የቀራቸው ቀይ ቀበሮዎቹ
May 23, 2026 392
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ወደ ወሳኝ ምዕራፍ ተሸጋግሯል። 16 ሀገራት በአራት ምድቦች ተከፍለው ጨዋታቸውን አድርገዋል። ከየምድቡ አንደኛ እና ሁለተኛ የወጡ ስምንት ሀገራት በኳታር ለሚካሄደው 20ኛው ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ አልፈዋል። በተጨማሪም ከየምድቡ ሶስተኛ የወጡ አራት ሀገራት የመለያ ጨዋታ አድርገው ቀሪ አላፊ ብሔራዊ ቡድኖች ይለያሉ። በውድድሩ ላይ እየተሳተፈ የሚገኘው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድንም በምድብ አንድ በአራት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ ወደ መለያ ጨዋታው ተሸጋግሯል። ብሔራዊ ቡድኑ በምድቡ የመጨረሻ ጨዋታ ቱኒዚያን 1 ለ 0 መርታቱ ወደ ወሳኝ ምዕራፍ አሸጋግሮታል። ቀይ ቀበሮዎቹ ለዓለም ዋንጫው ለማለፍ ከሞዛምቢክ ጋር ዛሬ ከምሽቱ አንድ ሰዓት በመሐመድ ስድስተኛ ኮምፕሌክስ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በምድብ ሶስት ተደልድሎ ጨዋታውን ያደረገው የሞዛምቢክ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በአራት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁ ይታወቃል። የሞዛምቢክ ቡድን በመጨረሻ የምድብ ጨዋታው አንጎላን 2 ለ 1 በማሸነፍ ለመለያ ጨዋታ ደርሷል። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ሞዛምቢክን ማሸነፍ ከቻለ በኳታር አስተናጋጅነት ለሚከናወነው 20ኛው ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ያልፋል። ቡድኑ ለዓለም ዋንጫ ካለፈ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ይሆናል። ቀይ ቀበሮዎቹ ለጨዋታው የመጨረሻ ልምምዳቸውን ትናንት ማድረጋቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙም አመልክቷል። አጥቂው ዳዊት ካሳው በውድድሩ ላይ በተመለከታቸው ሁለት ቢጫ ካርዶች ምክንያት በዛሬው ጨዋታ ላይ አይሰለፍም። አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር ከጨዋታው በፊት በሰጡት አስተያየት ለኢትዮጵያ ህዝብ በእግር ኳስ ደስታ መስጠት እንፈልጋለን ሲሉ ገልጸዋል። የቡድኑ ተጫዋቾችን ኢትዮጵያ ለዓለም ዋንጫ እንድታልፍ ቁርጠኛ ናቸው፤ ለማሸነፍ ወደ ሜዳ እንገባለን ብለዋል። በሌላኛው የመለያ መርሐ ግብር ጋና ከዩጋንዳ ምሽት አራት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። አዘጋጇ ሞሮኮ፣ ግብጽ፣ ኮትዲቯር፣ ካሜሮን፣ ታንዛንያ፣ ማሊ፣ ሴኔጋል እና አልጄሪያ በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ ሀገራት ናቸው። 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ እስከ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በአፍሪካ ዋንጫው እየተሳተፉ ካሉ 16 ሀገራት መካከል 10ሩ በጥቅምት እና ህዳር ወር 2019 ዓ.ም በኳታር ለሚካሄደው 20ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ያልፋሉ። በዓለም ዋንጫው 48 ሀገራት ይሳተፋሉ።
ማይክል ካሪክ የማንቸስተር ዩናይትድ ቋሚ ዋና አሰልጣኝ ሆኖ ተሾመ
May 22, 2026 393
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ ማንቸስተር ዩናይትድ የቀድሞ ተጫዋቹን ማይክል ካሪክን የሁለት ዓመት ውል በመስጠት የክለቡ ቋሚ ዋና አሰልጣኝ አድርጎ መሾሙን አስታወቀ። የ44 ዓመቱ ማይክል ካሪክ ክለቡን በቋሚነት እንዲመራ የተመረጠው፣ የቀድሞው አሰልጣኝ ሩበን አሞሪም በተጠናቀቀው የፈረንጆቹ ጥር ወር ከኃላፊነታቸው መሰናበታቸውን ተከትሎ በጊዜያዊ አሰልጣኝነት በነበረው አጭር ቆይታ ያስመዘገበውን መልካም ውጤት ከግምት ውስጥ በማስገባት ነው። ካሪክ ቡድኑን ከተረከበ በኋላ ባሳየው ተከታታይ የውጤት መሻሻል ክለቡ በሚቀጥለው የውድድር ዘመን በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ መሳተፍ የሚችልበትን ደረጃ ማረጋገጥ መቻሉን የቢቢሲ ዘገባ ያመለክታል። ማንቸስተር ዩናይትድ ባለፈው እሁድ ከኖቲንግሃም ፎረስት ጋር ያደረገውን ጨዋታ 3 ለ 2 በሆነ ውጤት ማሸነፉን ተከትሎ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የደረጃ ሰንጠረዥ ሦስተኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁን አረጋግጧል። አሰልጣኙ ቡድኑን በጊዜያዊነት መምራት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ካደረጋቸው 16 ጨዋታዎች መካከል በ11ዱ ድል ቀንቶታል። ማንቸስተር ዩናይትድ ካሪክ በጥር 13 ቀን 2026 (እ.ኤ.አ) ከተሾመበት ጊዜ ጀምሮ 36 ነጥቦችን የሰበሰበ ሲሆን፣ ይህም በሊጉ ካሉ ክለቦች ሁሉ በወቅቱ ከፍተኛው የተሰበሰበ ነጥብ ሆኖ ተመዝግቧል። ይህንን ተከትሎም ካሪክ ለፕሪሚየር ሊጉ የዓመቱ ምርጥ አሰልጣኝ ሽልማት ከታጩት ስድስት እጩዎች ዝርዝር ውስጥ ተካቷል። ማይክል ካሪክ ሹመቱን አስመልክቶ በሰጠው አስተያየት፣ ከ20 ዓመታት በፊት ወደ ኦልድ ትራፎርድ ከመጣበት ጊዜ ጀምሮ የክለቡን ታላቅነት እንደሚረዳ ገልጾ፣ ይህንን ልዩ ክለብ በቋሚነት የመምራት ኃላፊነት በመስጠቱ ታላቅ ኩራት እንደተሰማው ተናግሯል። ባለፉት አምስት ወራት የተጫዋቾች ስብስብ ያሳየው የአንድነትና የጽናት መንፈስ የሚደነቅ መሆኑን ጠቅሶ፣ ወደፊት ክለቡን ወደ ቀድሞ ታላቅነቱ ለመመለስና ለትላልቅ ዋንጫዎች ለመፎካከር በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አስታውቋል። የቀድሞው አሰልጣኝ ሩበን አሞሪም በክለቡ በነበራቸው የ14 ወራት ቆይታ ማብቂያ ላይ በተመዘገቡ ደካማ ውጤቶች እና በታክቲክ ምርጫዎች ዙሪያ ከክለቡ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በነበራቸው አለመግባባት ሳቢያ ከኃላፊነታቸው መሰናበታቸው ይታወሳል። ማይክል ካሪክ እ.ኤ.አ በ2021 የቀድሞው አሰልጣኝ ኦሌ ጉናር ሶልሻየር ከተሰናበቱ በኋላም ቡድኑን ለሦስት ጨዋታዎች በጊዜያዊነት መምራቱ የሚታወስ ሲሆን፣ በአሁኑ ቆይታው በሜዳ ላይና ከሜዳ ውጪ ባሳየው አመራር የክለቡን ባለሥልጣናትና ደጋፊዎች አድናቆት አትርፏል። አዲሱ ቋሚ አሰልጣኝ ማይክል ካሪክ በማንቸስተር ዩናይትድ በነበረው የ12 ዓመታት የተጫዋችነት ዘመን አምስት የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫዎችን፣ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኤፍኤ ካፕ ማሸነፍ የቻለ የክለቡ ስኬታማ ተጫዋች እንደነበር ቢቢሲ በዘገባው አውስቷል።
ፔፕ ጋርዲዮላ ከ10 ዓመታት በኋላ ማንችስተር ሲቲን እንደሚለቅ ተረጋገጠ
May 22, 2026 345
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ የማንቸስተር ሲቲ ዋና አሰልጣኝ ፔፕ ጋርዲዮላ ከእሁዱ የአስቶንቪላ የሊጉ የመጨረሻ ጨዋታ በኋላ ክለቡን እንደሚለቅ ይፋ ሆኗል። ማንቸስተር ሲቲ የአሰልጣኙን መልቀቅ አረጋግጧል። ስፔናዊው አሰልጣኝ ፔፕ ጋርዲዮላ ባለፉት 10 የፕሪሚየር ሊግ የውድድር ዘመናት ክለቡን በመምራት ስድስት የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫዎችን ጨምሮ 17 ዋና ዋና ክብሮችን ማሳካት መቻሉን ቢቢሲ ዘግቧል። የ55 ዓመቱ አሰልጣኝ የመጨረሻ ጨዋታውን እሁድ በኢትሃድ ስታዲየም ከአስቶንቪላ ጋር እንደሚያደርግ ተገልጿል። ማንቸስተር ሲቲ የአሰልጣኙ ውል ከመጠናቀቁ አንድ ዓመት ቀደም ብሎ ለስንብቱ ዝግጅት እያደረገ እንደነበር ቢቢሲ ስፖርት በዘገባው አስታውሷል። አሰልጣኝ ጋርዲዮላ ስለ ስንብቱ በሰጠው አስተያየት "የምለቅበትን ምክንያት አትጠይቁኝ፤ ምንም አይነት የተለየ ምክንያት ባይኖርም የመልቀቂያዬ ጊዜ መድረሱን ግን በውስጤ አውቀዋለሁ" ብሏል። አክሎም "በዚህ ዓለም ላይ ዘላለማዊ የሚሆን ምንም ነገር የለም፤ ቢኖር ኖሮ እዚሁ እቆይ ነበር። ዘላለማዊ ሆኖ የሚቀረው ግን ስሜቱ፣ ሰዎቹ፣ ትዝታዎቹ እና ለክለቡ ያለኝ ፍቅር ብቻ ነው" ሲል ስሜቱን ገልጿል። አሰልጣኙ ከሳምንት በፊት ከሲቲ የመጨረሻ ዋንጫውን በኤፍኤ ካፑ አንስቷል። የ55 ዓመቱን ፔፕ ጋርዲዮላ ለመተካት ቀደም ሲል በማንቸስተር ሲቲ በረዳትነት የሰራውና የቀድሞው የቼልሲ አሰልጣኝ ኤንዞ ማሬስካ ቀዳሚው እጩ መሆኑ ተጠቁሟል። የጋርዲዮላ ከክለቡ የመልቀቅ ዜና ይፋ የሆነው ማንቸስተር ሲቲ የ2025-26 የፕሪሚየር ሊግ ዋንጫን በአርሰናል ከተቀማ ከሶስት ቀናት በኋላ ነው። ማንቸስተር ሲቲ ማክሰኞ ከቦርንማውዝ ጋር አቻ መለያየቱን ተከትሎ አርሰናል ከ22 ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ የፕሪሚየር ሊጉ ሻምፒዮን መሆን መቻሉ ይታወሳል።
ነገሌ አርሲ እና ምድረ ገነት ሽሬ ነጥብ ተጋሩ
May 21, 2026 688
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 33ኛ ሳምንት ነገሌ አርሲ እና ምድረ ገነት ሽሬ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ተካሄዷል። ጨዋታውን ተከትሎ ነገሌ አርሲ በ52 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ነገሌ አርሲ የሁለተኝነት ደረጃን ከመቻል የመረከብ እና ከሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማጥበብ እድል አልተቀመበትም። ምድረ ገነት ሽሬ በ37 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ የ33ኛ ሳምንት ጨዋታዎች የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና አርባምንጭ ከተማን 3 ለ 0 ሲረታ አዳማ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 33ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ከኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በኋላ ከግንቦት 20 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ይካሄዳል።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
May 21, 2026 344
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና አርባምንጭ ከተማን 3 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ መስፍን ታፈሰ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር የአርባምንጭ ከተማው ኤፍሬም ታምራት በራሱ ላይ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በ14 ጎሎች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የሚመራው የሲዳማ ቡናው አጥቂ አቤል ያለው ባጋጠመው ጉዳት ምክንያት ወደ ህክምና ስፍራ ተወስዷል። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሲዳማ ቡና በ58 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ መቻል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ አድርጓል። በሊጉም 16ኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 14ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ29 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር አዳማ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ውጤቱን ተከትሎ አዳማ ከተማ በ39 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ40 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ33ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ ግብር ነገሌ አርሲ ከምድረ ገነት ሽሬ ምሽት 12 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና በሊጉ ግርጌ ከሚገኘው አርባምንጭ ከተማ ጋር ይጫወታል
May 21, 2026 341
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከሲዳማ ቡና በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አርባምንጭ ከተማ በ29 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ሲዳማ ቡና በ55 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ያላሸነፈው አርባምንጭ ከተማ ማሸነፍ በሊጉ የመቆየት ተስፋውን ለማለምለም የሚያስችለውን ሶስት ነጥብ እንዲያገኝ ያደርገዋል። ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ላይ ከድል የራቀው ሲዳማ ቡና ዛሬ ካሸነፈ ከተከታዩ መቻል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ ያደርጋል። ጨዋታው ለሁለቱም ቡድኖች ወሳኝ የሚባል ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ነገሌ አርሲ ከምድረ ገነት ሽሬ ምሽት 12 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ነገሌ አርሲ በ51 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ምድረ ገነት ሽሬ በ36 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ32ኛ ሳምንት በመቻል የ4 ለ 0 ሽንፈት ያስተናገደው ነገሌ አርሲ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ እና በዋንጫ ፉክክሩ ለመቆየት ሶስት ነጥብ ማግኘት ይኖርበታል። በተመሳሳይ በ32ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 ያሸነፈው ምድረ ገነት ሽሬ በዛሬው ጨዋታ ድል ከቀናው ከወራጅ ቀጠና ሊወጣበት የሚችልበት እድል ሊፈጠር ይችላል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። አዳማ ከተማ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። አዳማ ከተማ በ38 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ39 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር አዳማ ከተማ በፋሲል ከነማ የ3 ለ 1 ሽንፈት ሲያስተናግድ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 ረቷል። ጨዋታው ለሁለቱም ቡድኖች ከወራጅ ቀጠና ስፍራ ፈቀቅ ለማለት ወሳኝ የሚባል ነው። የዛሬ መርሐ ግብሮች ዋንጫ ለማንሳት እና ላለመውረድ በሚደረገው ፉክክር ላይ ተጽእኖ የሚያሳድሩ ናቸው።
አስቶንቪላ የዩሮፓ ሊግ ዋንጫን አነሳ
May 21, 2026 377
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በዩሮፓ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ አስቶንቪላ ፍራይበርግን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በቱርኪዬ ኢስታንቡል በሚገኘው ቲውፕራሽ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዩሪ ቲሊማንስ፣ ኢሚሊያኖ ቡንዲያ እና ሞርጋን ሮጀርስ የማሸነፊያ ጎሎቹን አሳርፈዋል። በጨዋታው አስቶንቪላ የተሻለ ብልጫ የወሰደ ሲሆን ተጨማሪ ጎሎችን የማስቆጠር እድሎችን መጠቀም አልቻለም። የአስቶንቪላ ደጋፊ የሆኑት የዌልስ ልዑል ዊሊያምስ ጨዋታውን በስታዲየም በመገኘት ተከታትለዋል። ውጤቱን ተከትሎ አስቶንቪላ የዘንድሮው የዩሮፓ ሊግ አሸናፊ ሆኗል። ቪላ እ.አ.አ በ1982 የዩሮፓ ካፕ (የአሁኑ ሻምፒዮንስ ሊግ) ካነሳ 44 ዓመታት በኋላ ሌላኛውን የአውሮፓ ክብር ተቀዳጅቷል። ቡድኑ እ.አ.አ በ1996 የሊግ ካፕ ዋንጫውን ካነሳ በኋላ የመጀመሪያ ዋንጫውን አሳክቷል። ስፔናዊው የአስቶንቪላ አሰልጣኝ ኡናይ ኤምሬ ከተለያዩ ክለቦች ጋር ዩሮፓ ሊግ ዋንጫን አምስት ጊዜ በማንሳት አዲስ ታሪክ ጽፈዋል። ኤምሬ "የዩሮፓ ሊግ ንጉስ" የሚል የክብር ስም ተሰጥቷቸዋል። የዩሮፓ ሊግ አሸናፊው አስቶንቪላ በሊጉ አምስተኛ ደረጃን ይዞ ካጠናቀቀ በቀጣዩ ዓመት በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሚሳተፉ የእንግሊዝ ክለቦች ብዛት ወደ ስድስት ያድጋል። ፍራይበርግ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ዋንጫ የማንሳት ህልሙ ሳይሳካ ቀርቷል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ከሞዛምቢክ ጋር ይጫወታል
May 20, 2026 443
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦ 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ይገኛል። በውድድሩ ላይ እየተሳተፈ የሚገኘው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በምድብ አንድ በአራት ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ ለዓለም ዋንጫ የመለያ ጨዋታ አልፏል። ቡድኑ ወደ መለያ ጨዋታው የተሸጋገረው ትናንት ቱኒዚያን 1 ለ 0 ማሸነፉን ተከትሎ ነው። ብሔራዊ ቡድኑ ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ቅዳሜ ግንቦት 15 ቀን 2018 ዓ.ም ከሞዛምቢክ ጋር ይጫወታል። ሞዛምቢክ በምድብ ሶስት ሶስተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በተያያዘም በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው ብሔራዊ ቡድን ከቱኒዚያው ጨዋታ በኋላ ዛሬ ልምምድ ማድረጉን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ድሬዳዋ ከተማ ነጥብ ተጋሩ
May 20, 2026 318
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ድሬዳዋ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሩዋንዳዊው ፓትሪክ ሲቦማና በ16ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ኢትዮ ኤሌክትሪክ መሪ ሆኗል። አስቻለው ታመነ በ63ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ድሬዳዋ ከተማን አቻ ያደረገውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ46 ነጥብ ከነበረበት ስድስተኛ ደረጃ ወደ አራተኛ ከፍ ብሏል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ድሬዳዋ ከተማ በ35 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ33ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና ፋሲል ከነማን 2 ለ 1 ሲረታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሃዋሳ ከተማን፣ መቀሌ 70 እንደርታ ሸገር ከተማን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል።