ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ማንችስተር ሲቲ ለስምንተኛ ጊዜ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን አነሳ
May 16, 2026 16
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኤፍኤ ካፕ የፍጻሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ ቼልሲን 1 ለ 0 አሸንፏል። በዌምብሌይ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንቶዋን ሴሜኒዮ በ71ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ሴሜኒዮ የግል ድንቅ ብቃቱን ተጠቅሙ በተለምዶ ‘ቄንጠኛ’ በሚባል መልኩ ያስቆጠራት ጎል አስደማሚ የሚባል ነው። ማንችስተር ሲቲ በተጋጣሚው ላይ ብልጫ ወስዶ ተጫውቷል። ድሉን ተከትሎ ማንችስተር ሲቲ የኤፍኤ ካፑን ዋንጫ ለስምንት ጊዜ አንስቷል። ውሃ ሰማያዊዎቹ ከሶስት ዓመታት በኋላ አንጋፋውን ውድድር አሸንፈዋል። ሲቲ ከካራባኦ ካፕ በኋላ በዘንድሮው የውድደር ዓመት ሁለተኛ ዋንጫውን አገኝቷል። በአንጻሩ ቼልሲ ለዘጠነኛ ጊዜ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን የማንሳት ህልሙ አልተሳካም። ሰማያዊዎቹ ለመጨረሻ ጊዜ ውድድሩን ያሸነፈው እ.አ.አ 2018 ነው። ቼልሲ ዋንጫውን ቢያነሳ ዩሮፓ ሊግ የመግባት እድል ያገኝ ነበር።
ወልዋሎ አዲግራት ዩኒርሲቲ ድል ሲቀናው ሃዋሳ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ አቻ ተለያይተዋል
May 16, 2026 82
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መካሄዱን ቀጥሏል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። ጋናዊው ኮንኮኒ ሃፊዝ እና እንዳልካቸው ጥበቡ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። አቤል ሀብታሙ የኢትዮ ኤሌክትሪክን ብቸኛ ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከሁለት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ39 ነጥብ ደረጃውን ከ16ኛ ወደ 15ኛ ከፍ አድርጓል። በሊጉም ዘጠነኛ ድሉን አሳክቷል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ45 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተደረገው ሌላኛው መርሐ ግብር ሃዋሳ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ሃዋሳ ከተማ በ45 ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ዘጠኝ የሊጉ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ በውጤት ማጣት ቀውስ ይገኛል። አርባምንጭ ከተማ በ29 ነጥብ የመጨረሻው 20ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሲሆን ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም።
ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ መቆየቱን ሲያረጋግጥ አዲስ አበባ ከተማ ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ ወርዷል
May 16, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ሸገር ከተማ እና ይርጋጨፌ ቡና ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ተካሄዷል። የይርጋጨፌ ቡናዋ ግብ ጠባቂ የኔነሽ አበበ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ይርጋጨፌ ቡና በ19 12ኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ በሊጉ መቆየቱን አረጋግጧል። በአንጻሩ በ15 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አዲስ አበባ ከተማ ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ ወርዷል። አርባምንጭ ከተማ አስቀድሞ ወደ ከፍተኛ ሊግ መውረዱ ይታወቃል። ሸገር ከተማ በበኩሉ በ48 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን በመያዝ የውድድር ዓመቱን አጠናቋል። በሌላኛው መርሐ ግብር ድሬዳዋ ከተማ አዳማ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ድሬዳዋ ከተማ ድል ቀንቶታል
May 16, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ድሬዳዋ ከተማ አዳማ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ዝናሽ ሰለሞን እና ፊርማዬ ከበደ የማሸነፊያ ግቦቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አህላም ሲራጅ የአዳማ ከተማን ብቸኛ ጎል አስቆጥራለች። የድሬዳዋ ከተማዋ አምበል ሊና መሐመድ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ ስምንተኛ ድሉን ያስመዘገበው ድሬዳዋ ከተማ በ28 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዞ የውድድር ዓመቱን አጠናቋል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 14ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዳማ ከተማ በበኩሉ በ22 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል።
ኢትዮጵያ በ20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር በሁለቱም ጾታዎች የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 16, 2026 141
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛ የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ አምስተኛ ቀኑን ይዟል። በወንዶች 20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር አትሌት ምስጋናው ዋቁማ አሸንፏል። ውድድሩን በአንደኝነት በማጠናቀቅ በአፍሪካ ሻምፒዮና መድረክ በተከታታይ ለሁለተኛ ጊዜ በማሸነፍ ክብሩን አስጠብቋል። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት አብዱልሰላም አብዱልዋሂብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ የነሐስ ሜዳሊያ ለሀገሩ አስገኝቷል። በሴቶች 20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር ደግሞ አትሌት ውብአለም ሽጉጤ በቀዳሚነት አጠናቃ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። በዚሁ ውድድር ላይ የተካፈሉት አትሌት ሕይወት አምባው አራተኛ እንዲሁም አትሌት ማሬ ቢተው ስምንተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድራቸውን አጠናቀዋል። ውጤቶቹን ተከትሎ ኢትዮጵያ ያገኘቻቸው የወርቅ ሜዳሊያዎች ብዛት አምስት ደርሰዋል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው አምስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና አምስት የነሐስ በድምሩ 11 ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። ሻምፒዮናው ነገ ይጠናቀቃል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
May 16, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ36 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ45 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ማግኘት ያልቻለው ወልዋሎ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና ስፍራ ፈቀቅ እንዲል ያደርገዋል። በ31ኛ ሳምንት ፋሲል ከነማን 3 ለ 1 የረታው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ካሸነፈ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ሃዋሳ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባለፉት ስምንት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ በ44 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ28 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ በ31ኛ ሳምንት በወላይታ ድቻ የ3 ለ 2 ሽንፈት አስተናግዷል። ሃዋሳ ከተማ ከድል ጋር ለመታረቅ፣ አርባምንጭ ከተማ ላለመውረድ በሚያደርገው ትግል ሶስት ነጥብ ለማግኘት የሚያደርጉት ፍልሚያ ትኩረትን ስቧል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ፋሲል ከነማ ከአዳማ ከተማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ፋሲል ከነማ በ43 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። አዳማ ከተማ በ38 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ድል ያልቀናው ፋሲል ከነማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። በ31ኛ ሳምንት ምድረ ገነት ሽሬን 4 ለ 0 በመርታት ከስምንት ጨዋታዎች በኋላ ሶስት ነጥብ ያገኘው አዳማ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን የሞሮኮ አቻውን ይገጥማል
May 16, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት የሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ አራተኛ ቀኑን ይዟል። በምድብ አንድ የሚገኘው የኢትዮጵያ ታዳጊ ብሔራዊ ቡድን ሁለተኛ ጨዋታውን ዛሬ ከአዘጋጇ ሞሮኮ ጋር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ ኮምፕሌክስ ያደርጋል። ብሔራዊ ቡድኑ በመጀመሪያ ጨዋታው ከግብጽ ጋር ያለ ግብ አቻ በመውጣት አንድ ነጥብ አግኝቷል። ቡድኑ በጨዋታው ላይ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ አድርጓል። አዘጋጇ ሞሮኮ በመጀመሪያ ጨዋታ ቱኒዚያን 3 ለ 0 በማሸነፍ ምድቡን እየመራች ነው። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመዋር ቡድን ከምድቡ ለማለፍ እና በኳታር ለሚደረገው ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ የማለፍ ህልሙን ለማሳካት ከዛሬው ጨዋታ ሶስት ነጥብ ማግኘት ይጠበቅበታል። የአጥቂ መስመሩ የሚፈጠሩ የግብ ዕድሎችን ወደ ውጤት የመቀየር አቅሙን ማሳደግ ይኖርበታል። ብሔራዊ ቡድኑ ከጨዋታው በፊት የመጨረሻ ልምምዱን በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ አካዳሚ ማድረጉንና ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በዚሁ ምድብ ከቀኑ 10 ሰአት ላይ ቱኒዚያ ከግብጽ በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ ኮምፕሌክስ ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊጉ የ25ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን መርሐ ግብር
May 16, 2026 132
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከጠዋቱ ሶስት ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ባለፉት ሰባት ጨዋታዎች ከድል የራቀው አዳማ ከተማ በ22 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በ25 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሁለቱም ቡድኖች ዓመቱን አሸናፊነት ለማጠናቀቅ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ሸገር ከተማ ከይርጋጨፌ ቡና ከረፋዱ አምስት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሸገር ከተማ በ47 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ይርጋጨፌ ቡና በ18 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ26ኛ ሳምንት በቦሌ ክፍለ ከተማ 2 ለ 0 የተሸነፈው ሸገር ከተማ ዓመቱን በድል ለመቋጨት ይፋለማል። ይርጋጨፌ ቡና ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል።
የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ማን ያነሳል? ቼልሲ ወይስ ማንችስተር ሲቲ?
May 16, 2026 138
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ ቼልሲ እና ማንችስተር ሲቲ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ለማንሳት ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታው ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ 90 ሺህ ተመልካች በሚያስተናግደው ዌምብሌይ ስታዲየም ይካሄዳል። ቼልሲ ሊድስ ዩናይትድን እንዲሁም ማንችስተር ሲቲ ሳውዝሃምተንን በማሸነፍ ለፍጻሜው ማለፋቸው የሚታወስ ነው። ሁለቱ ክለቦች በኤፍኤ ካፕ ታሪካቸው ለ10ኛ ጊዜ የሚገናኙ ሲሆን፣ ቀደም ባሉት ዘጠኝ ግንኙነቶች ማንችስተር ሲቲ ስድስት ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። በአንጻሩ ቼልሲ በቀሪዎቹ ሶስት ጨዋታዎች ድል ቀንቶታል። በዘጠኙ ጨዋታዎች ላይ ማንችስተር ሲቲ 16 ግቦችን ሲያስቆጥር ቼልሲ ዘጠኝ ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቡድኖቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተገናኙት እ.አ.አ በ1915 በሶስተኛ ዙር ላይ ሲሆን ቼልሲ 1 ለ 0 አሸንፏል። እ.አ.አ በ2024 ለመጨረሻ ጊዜ በተገናኙበት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ 1 ለ 0 በመርታት ለፍፃሜው አልፏል። ቼልሲ ለኤፍኤ ካፕ ፍጻሜ ሲያልፍ ይህ ለ17ኛ ጊዜው ነው። የምዕራብ ለንደኑ ክለብ እስከ አሁን ስምንት ጊዜ የዋንጫው ባለቤት መሆን ችሏል። ማንችስተር ሲቲ ለ14ኛ ጊዜ ለፍጻሜ የደረሰ ሲሆን፣ እስካሁን ባደረጋቸው የፍጻሜ ጨዋታዎች ሰባት ጊዜ ዋንጫውን አንስቷል። ሁለቱ ቡድኖች ታሪካዊውን ዋንጫ ለማንሳት የሚያደርጉት ፍልሚያ ፣ ብርቱ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ቼልሲ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ካነሳ ለዩሮፓ ሊግ ማለፉን ያረጋግጣል። የ40 ዓመቱ ዳረን ኢንግላንድ ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። 154 ዓመታትን ያስቆጠረው ኤፍኤ ካፕ የዓለማችን እጅግ አንጋፋው የእግር ኳስ ውድድርነው።
አስቶንቪላ ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ማለፉን አረጋገጠ
May 16, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት የመጀመሪያ መርሐ ግብር አስቶንቪላ ሊቨርፑልን 4 ለ 2 ረቷል። በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኦሊ ዋትኪንስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሞርጋን ሮጀርስ እና ጆን ማጊን ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቨርጅል ቫን ዳይክ ለሊቨርፑል ጎሎቹን አስቆጥሯል። በሊቨርፑሉ አማካይ ዶምኒክ ስቦዝላይ በተሰራው ስህተት ኦሊ ዋትኪንስ ያስቆጠረው ጎል የጨዋታው ቁልፍ ክስተት ነበር። ሊቨርፑል በጨዋታው የሰራቸው ስህተቶች ዋጋ አስከፍሎታል። ጨዋታው አዝናኝ እንቅስቃሴ የተደረገበት ሲሆን አስቶንቪላ ግልጽ የግብ እድሎችን በተሻለ ሁኔታ ፈጥሯል። በሊጉ 18ኛ ድሉን ያስመዘገበው አስቶንቪላ በ62 ነጥብ አራተኛ ደረጃን በመያዝ አንድ ጨዋታ እየቀረው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን አረጋግጧል። በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሊቨርፑል በ59 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመሳተፍ በ38ኛ ሳምንት ብሬንትፎርድን ማሸነፍ ይጠበቅበታል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ተጨማሪ ሜዳሊያ አገኘች
May 15, 2026 307
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና በጋና አክራ መካሄዱን ቀጥሏል። ማምሻውን በተካሄደው የ10000 ሜትር የሴቶች የፍጻሜ ውድድር አትሌት አሰፉ አብርሃ ሶስተኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳሊያ አግኝታለች። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው ሶስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና አራት የነሐስ በድምሩ ስምንት ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። ሻምፒዮናው እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
ሃዋሳ ከተማ በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ አራተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቀቀ
May 15, 2026 131
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሃዋሳ ከተማ ቦሌ ክፍለ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ታደለች አብርሃም በ53ኛው ደቂቃ ግቡን አስቆጥራለች። የሃዋሳ ከተማዋ ትዕግስት አበራ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ 15ኛ ድሉን ያስመዘገበው ሃዋሳ ከተማ በ52 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዞ የውድድር ዓመቱን አጠናቋል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ሰባተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ43 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረጉ የ25ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ጨዋታዎች ሲዳማ ቡና አርባምንጭ ከተማን 3 ለ 0፣ ባህር ዳር ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፈዋል።
ባህር ዳር ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድል ቀንቷቸዋል
May 15, 2026 121
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተካሄደዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ባህር ዳር ከተማ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ፍፁም ፍትዓለው እና አንተነህ ተፈራ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን ያስመዘገበው ባህር ዳር ከተማ በ44 ነጥብ ደረጃውን ከ9ኛ ወደ 6ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ34 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም የተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሸገር ከተማን 2 ለ 1 ረቷል። አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል ለንግድ ባንክ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቢንያም ፍቅሩ የሸገር ከተማን የማስተዛዘኝ ግብ አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ድሉን ያገኘው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ41 ነጥብ ከነበረበት 14ኛ ደረጃ ወደ 11ኛ ከፍ ብሏል። በሊጉ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሸገር ከተማ ደግሞ በ40 ነጥብ ከ12ኛ ደረጃ ወደ 13ኛ ወርዷል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጫዋቾቹ አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል በሊጉ ያስቆጠሩትን የግብ መጠን በተመሳሳይ 11 በማድረስ፣ በ14 ግቦች የከፍተኛ ግብ አግቢነቱን ደረጃ እየመራ የሚገኘውን የሲዳማ ቡናውን አቤል ያለውን ይከተላሉ። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ የ32ኛ ሳምንት ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ ተለያይተዋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ሲዳማ ቡና ድል ቀንቶታል
May 15, 2026 181
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ሲዳማ ቡና አርባምንጭ ከተማን 3 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ኤልሳ ብርሃኑ፣ ምርጥነሽ ዮሐንስ እና ምትኬ ብርሃኑ የማሸነፊያ ግቦች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የሲዳማ ቡናዋ ምትኬ ብርሃኑ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጣለች። በሊጉ 11ኛ ድሉን ያስመዘገበው ሲዳማ ቡና በ38 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ የወረደው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። በውድድር ዓመቱ 20ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በሊጉ ያሸነፋው ጨዋታዎች ብዛት ሁለት ብቻ ናቸው። ይህም አርባምንጭ ከተማን በሊጉ አነስተኛ ድል ያስመዘገበ ቡድን አድርጎታል።
መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድን ነጥብ ተጋሩ
May 15, 2026 117
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጋናዊው አብዱል ጋንዩ በ67ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል መድን መሪ ሆኗል። ብርሃኑ አዳሙ በ84ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፈው ግብ ለመቀሌ 70 እንደርታ ወሳኝ አንድ ነጥብ አስገኝቷል። መቀሌ 70 እንደርታ በ31 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ከሶስት ተከታታይ ድሎች በኋላ አቻ የወጣው ኢትዮጵያ መድን በ41 ነጥብ ደረጃውን ከ11ኛ ወደ 9ኛ ከፍ አድርጓል።
ባህር ዳር ከተማ የውድድር ዓመቱን በድል ቋጭቷል
May 15, 2026 130
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ባህር ዳር ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማን 2 ለ 1 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አስቴር ደግአረገ እና ወርቅነሽ መሰለ የማሸነፊያ ጎሎቹን አስቆጥረዋል። ረድኤት ዳንኤል ለልደታ ክፍለ ከተማ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፋለች። የባህር ዳር ከተማዋ ወርቅነሽ መሰለ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። በሊጉ ሰባተኛ ድሉን ያስመዘገበው ባህር ዳር ከተማ ደረጃውን ከ11ኛ ወደ 10ኛ ከፍ አድርጓል። ዓመቱንም በድል አጠናቋል። በውድድር ዓመቱ 16ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ልደታ ክፍለ ከተማ በተመሳሳይ 22 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ ዘጠነኛ ደረጃን ይዟል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍፃሜ መርሐ ግብር የሚደረግባቸው ቀናቶች ይፋ ሆኑ
May 15, 2026 144
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የግማሽ ፍፃሜ ድልድል ትናንት መውጣቱ ይታወቃል። በእጣው መሰረት ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ መድን፣ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ 70 እንደርታ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ጨዋታዎቹ የሚደረግባቸውን ቀናት እና የመጫወቻ ሜዳ ዛሬ ይፋ አድርጓል። በዚሁ መሰረት ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከመቀሌ 70 እንደርታ ግንቦት 17፣ ሲዳማ ቡና ከኢትዮጵያ መድን ግንቦት 18 በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ።
በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የሚሳተፉባቸው ውድድሮች
May 15, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ አራተኛ ቀኑን ይዟል። ምሽት 2 ሰዓት ከ05 ላይ የ10000 ሜትር ሴቶች የፍጻሜ ውድድር ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ አሰፉ አብርሃ፣ ስምረት በርሄ እና ዘይን አየልኝ ኢትዮጵያን ወክለው ይሳተፋሉ። አትሌት ዘይን አየልኝ በ5000 ሴቶች የነሐስ ሜዳሊያ ማግኘቷ ይታወሳል። አትሌት ጌታሁን ታደሰ ምሽት 1 ሰዓት ከ45 ላይ በሚካሄደው የወንዶች የ110 ሜትር መሰናክል የማጣሪያ ውድድር ላይ ይሳተፋል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው ሶስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና ሶስት የነሐስ በድምሩ ሰባት ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። የአትሌቲክስ ሻምፒዮናው ከነገ በስቲያ ይጠናቀቃል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች
May 15, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። የዕለቱ ቀዳሚ መርሐ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድንን ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ያገናኛል። መቀሌ 70 እንደርታ በ30 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ኢትዮጵያ መድን በ40 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች አሸንፏል። ጨዋታው መቀሌ 70 እንደርታ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ኢትዮጵያ መድን በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው። ድሬዳዋ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ያላገኘው ድሬዳዋ ከተማ በ34 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሉ። ባህር ዳር ከተማ በ41 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ባህር ዳር ከተማ በዘንድሮው የውድድር ዓመት በርካታ የአቻ ውጤቶችን (17 ጊዜ) ያስመዘገበ ቡድን ነው። ሁለቱም ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ38 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሸገር ከተማ በ40 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኢትዮጵያ መድን የ2 ለ 1 ሽንፈት ሲያስተናግድ ሸገር ከተማ የሊጉን መሪ ሲዳማ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታው ንግድ ባንክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ሸገር ከተማ በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የማጠናቀቂያ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ
May 15, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይደረጋሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ልደታ ክፍለ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ይጫወታሉ። ልደታ ክፍለ ከተማ በ22 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በ19 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በ26ኛ ሳምንት ወራጁን አርባምንጭ ከተማን 4 ለ 1 ያሸነፈው ልደታ ክፍለ ከተማ ዓመቱን በድል ለመቋጨት ይጫወታል። በ26ኛ ሳምንት በአዲስ አበባ ከተማ 3 ለ 1 የተሸነፈው ባህር ዳር ከተማ ዓመቱን ድል ለማሳረግ ወደ ሜዳ ይገባል። በሌላኛው መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና በ35 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ መውረዱ የተረጋገጠው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። በ25ኛ ሳምንት ይርጋጨፌ ቡና ያለ ግብ አቻ የተለያየው ሲዳማ ቡና ዓመቱን በማሸነፍ ለመፈጸም ይጫወታል። ከፕሪሚየር ሊጉ ለወረደው አርባምንጭ ከተማ ጨዋታው ከመርሐ ግብር ማሟያነት የዘለለ ትርጉም የለውም። ሃዋሳ ከተማ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሃዋሳ ከተማ በ49 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ43 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች ዓመቱን በድል ለማጠናቀቅ የሚያደርጉት ፍልሚያ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ66 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በተመሳሳይ 66 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰሎሞን በ24 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራች ይገኛል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ ደግሞ በ20 ግቦች ተከታዩን ስፍራ ይዛለች።