ስፖርት - ኢዜአ አማርኛ
ስፖርት
ጃማይካ እና ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ የፍጻሜ ጨዋታ አለፉ
Mar 27, 2026 31
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ የዓለም የክፍለ አህጉራት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች በሜክሲኮ ተካሄደዋል። ዛሬ ማለዳ በአክሮን ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጃማይካ ኒው ካሌዶኒያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ባይሊ ካዳማርቴሪ በ18ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ጃማይካ በኳስ ቁጥጥር እና የግብ እጅሎችን በመፍጠር ከተጋጣሚዋ ኒው ካሌዶኒያ ተሽላ ተገኝታለች። ትናንት ከእኩለ ሌሊት በኋላ በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ቦሊቪያ ሱሪናምን 2 1 ረታለች። በቢቢቪኤ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሞሰስ ፓኒያጉአ በጨዋታ እና ሚጉዌል ቴርሴሮስ በፍጹም ቅጣት ምት የማሸነፊያ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ሊያም ቫን ጌልደርን ለሱሪናም ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ውጤቶቹን ተከትሎ ጃማይካ እና ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ፍጻሜ አልፈዋል። ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ከጃማይካ እና ኢራቅ ቦሊቪያ ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ መጋቢት 18 ቀን 2018 ዓ.ም በሜክሲኮ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ ያላቸው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ኢራቅ አስቀድመው ለፍጻሜው ጨዋታ ማለፋቸው ይታወቃል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ትጫወታለች
Mar 27, 2026 45
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የመጀመሪያ ጨዋታዋን ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ዛሬ ታደርጋለች። የሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች ጨዋታ በሞሮኮ ኤል አብዲ ስታዲየም ምሽት 12 ሰዓት ላይ ይካሄዳል። 36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እ.አ.አ ጁን 2027 በኬንያ ፣ ዩጋንዳና ታንዛንያ ጣምራ አዘጋጅነት ይከናወናል። በአፍሪካ ዋንጫ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ 12 አገራት የደርሶ መልስ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ከጨዋታዎቹ መካከል ኢትዮጵያ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር የምታደርገው ይገኝበታል። የሁለቱ ሀገራት የመጀመሪያ ጨዋታ ዛሬ ይካሄዳል። ብሄራዊ ቡድኖቹ በውድድር ጨዋታዎች ሲገናኙ የአሁኑ ለሶስተኛ ጊዜ ነው። ከዚህ ባደረጓቸው ሁለት ጨዋታዎች በተመሳሳይ አንድ ጊዜ አሸንፈዋል። ሩሲያ እ.አ.አ በ2018 ባዘጋጀቸው 21ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የአፍሪካ ዞን ማጣሪያ ላይ ተገናኝተው ኢትዮጵያ በድምር ውጤት 3 ለ 1 በማሸነፍ ቀጣዩን ዙር መቀላቀሏ የሚታወስ ነው። በመጀመሪያው ጨዋታ ሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ 1 ለ 0 ስታሸንፍ ኢትዮጵያ በመልሱ ጨዋታ 3 ለ 0 አሸንፋለች። ዮሐንስ ሳህሌ በታህሳስ ወር 2018 ዓ.ም በሁለት ዓመታት የውል ጊዜ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው በይፋ መሾማቸው ይታወቃል። አዲሱ አሰልጣኝ የመጀመሪያ ጨዋታቸውን ዛሬ ያደርጋሉ። አሰልጣኝ ዮሐንስ ለጨዋታዎቹ ጥሪ ያደረጉላቸው ተጫዋቾች ለስምንት ቀናት በአዲስ አበባ ልምምዳቸውን አድርገዋል። ብሄራዊ ቡድኑ የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት ማምሻውን በኤል አብዲ ስታዲየም ማድረጉን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በ47 ዓመቱ ፓርቹጋላዊ ሪካርዶ ሞናሳንቶ የሚመራው የሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ብሄራዊ ቡድን ለጨዋታ ለአንድ ሳምንት ያህል ልምምዱን አከናውኗል። በፊፋ ወርሃዊ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ ሳኦ ቶሜ እና ፕሪንሲፔ 189ኛ ደረጃን ይዛለች። ኢትዮጵያ 147ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች። ሁለቱ ብሄራዊ ቡድኖች የመልስ ጨዋታቸውን መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ያደርጋሉ። በደርሶ መልስ የሚያሸንፈው ሀገር ወደ ምድብ ድልድል ምዕራፍ ማለፉን ያረጋግጣል።
ቱርክዬ ወሳኝ ድል ተቀዳጅታለች
Mar 26, 2026 140
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የአውሮፓ የጥሎ ማለፍ የመጀመሪያ መርሐ ግብር ቱርክዬ ሮማንያን 1 ለ 0 አሸንፋለች። ማምሻውን ኢስታንቡል በሚገኘው ቱርፓስ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፌርዲ ካዲኦግሉ በ53ኛው ደቂቃ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በጨዋታው ቱርክዬ ብልጫ ወስዳ ተጫውታለች። ውጤቱን ተከትሎ ቱርክዬ ወደ ጥሎ ማለፉ የመጨረሻ ማጣሪያ ጨዋታ አልፋለች። ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ከስሎቫኪያ እና ኮሶቮ አሸናፊ ጋር መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ትጫወታለች። የ23ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ጥሎ ማለፍ ቀሪ ጨዋታዎች ማምሻውን መካሄዳቸውን ይቀጥላሉ። በጥሎ ማለፉ የሚያልፉ አራት ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ።
23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል በሐረር ከተማ ይካሄዳል
Mar 26, 2026 134
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው ሀገር አቀፍ የባህል ስፖርቶች ውድድር እና 19ኛው የባህል ስፖርቶች ፌስቲቫል ከመጋቢት 20 እስከ 27 ቀን 2018 ዓ.ም በሐረር ከተማ እንደሚካሄድ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታወቀ። የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የስፖርት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ መኪዩ መሐመድ ውድድሩንና ፌስቲቫሉን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል። ሚኒስትር ዴኤታው መንግስት ለስፖርት ልማት በሰጠው ልዩ ትኩረት በአዲሱ የስፖርት ፖሊሲ አማካኝነት የባህል ስፖርቶችን ለማልማት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ሁነቱ የኢትዮጵያን ህብረ ብሄራዊ አንድነት፣ ብዝሃነት እና አብሮነት የሚተዋወቅበት መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ህይወት መሐመድ በበኩላቸው ውድድሩና ፌስቲቫሉ ህብረተሰቡን በባህል ስፖርት ተሳታፊና ተጠቃሚ ከማድረግም ባሻገር የባህል ስፖርትን ማህበረሰብ አቀፍ የማድረግ አላማ እንዳለው ገልጸዋል። በውድድርና ፌስቲቫሉ ከአፍሪካ ባህል ስፖርቶች እና ጨዋታዎች ኮንፌዴሬሽን የተጋበዙ የክብር እንግዶች እንደሚታደሙበት ጠቁመዋል። በ11 የስፖርት አይነት በሚካሄደው ውድድርና ፌስቲቫል ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ ከ1500 በላይ ስፖርተኞች ይሳተፋሉ። ሁነቱ የኢትዮጵያ ባህል ስፖርት ፌዴሬሽን ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ነው። ውድድሩና ፌስቲቫሉ "የባህል ስፖርቶች ልማት ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ እንደሚካሄድ የሚኒስቴሩ መረጃ ያመለክታል።
ብሔራዊ ቡድኑ ከነገው ጨዋታ አስቀድሞ የመጨረሻ ልምምዱን አከናውኗል
Mar 26, 2026 146
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በ36ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከሳኦቶሜ እና ፕሪንሲፔ ጋር ነገ የመጀመሪያ የቅድመ ማጣሪያ ጨዋታውን ታደርጋለች። ብሔራዊ ቡድኑ ጨዋታው በሚደረግበት ኤል አብዲ ስታዲየም የመጨረሻ ልምምዱን ዛሬ ማምሻውን አከናውኗል። ሁሉም ተጫዋቾች በተሟላ ጤንነት ልምምዳቸውን ሰርተው ማጠናቀቃቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የኢትዮጵያ እና ሳኦቶሜ ጨዋታ ነገ ምሽት 12 ሰዓት ላይ በኤል ጀዲዳ ኤል አብዲ ስታዲየም ይከናወናል።
ድሬዳዋ ከተማ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 26, 2026 61
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ድሬዳዋ ከተማ አርባምንጭ ከተማን 1 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ የአርባምንጭ ከተማዋ መድሃኒት ዓለሙ በ79ኛው ደቂቃ በራሷ ላይ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥራለች። የድሬዳዋ ከተማዋ መዓዛ አብደላ የጨዋታው ኮከብ በመባል ተመርጣለች። ከአምስት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ድሬዳዋ ከተማ በ24 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ሰባተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በውድድር ዓመቱ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 10ኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ ባለፉት 14 የሊጉ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ይርጋጨፌ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 4 ለ 2፣ ቦሌ ክፍለ ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 አሸንፈዋል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ 21ኛ ሳምንት ተጠናቋል። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከመጋቢት 28 እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም በቱርክዬ በሚከናወነው የዩኤፋ የወዳጅነት ዋንጫ ዝግጅት እና ተሳትፎ ያደርጋል። በብሔራዊ ቡድኑ ተሳትፎ ምክንያት የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ እንደሚቋረጥ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
በሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ቦሌ ክፍለ ከተማ ድል ቀንቶታል
Mar 26, 2026 75
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ቦሌ ክፍለ ከተማ ባህር ዳር ከተማን 2 ለ 0 ረቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ምህረት በቀለ ሁለቱንም ግቦች አስቆጥራለች። ምህረት አየለ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል የተመለሰው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ34 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። በሊጉ ያሸነፋቸው ጨዋታዎች ብዛት ዘጠኝ ደርሰዋል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 15ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ባህር ዳር ከተማ በ16 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል።
ለዩኤፋ ፍሬንድሺፕ ካፕ ውድድር ለ22 ተጫዋቾች ጥሪ ቀረበ
Mar 26, 2026 70
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በቱርክዬ ለሚከናወነው የዩኤፋ ፍሬንድሺፕ ዋንጫ ውድድር አሰልጣኝ ቻለው ለሜቻ ለ22 ተጫዋቾች ጥሪ አድርገዋል። ስመኝሽ ፍቃዱ (አዳማ ከተማ) እና ሊንጎ ኦማን (ቦሌ ክፍለ ከተማ) ጥሪ የተደረገላቸው ግብ ጠባቂዎች ናቸው። በተከላካይ መስመር አሶሬ ሃይሶ (ባህር ዳር ከተማ )፣ ፍቅርአዲስ ገዛኸኝ ( ቦሌ ክፍለ ከተማ) ፣ ለምለም አስታጥቄ (ሃዋሳ ከተማ )፣ ሳባ ኃይለሚካኤል (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ቤተልሄም መስፍን (ሃዋሳ ከተማ)፣ ከአምላክነሽ ሃንኮ (ሃዋሳ ከተማ)፣ ዝናሽ ሰለሞን (ድሬዳዋ ከተማ) እና ወርቅነሽ ዘሪሁን (ሸገር ከተማ) ጥሪ ተደርጎላቸዋል። ቱሪስት ቱንጋ (አዳማ ከተማ) ዙፋን ደፈርሻ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ሚለን ጋይም (ቦሌ ክፍለ ከተማ)፣ ሜላት ጌታቸው (ቦሌ ክፍለ ከተማ)፣ ብርሃን ኃይለስላሴ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ) እና ጋብሬላ አበበ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ) ቡድኑን እንዲቀላቀሉ ጥሪ ቀርቦላቸዋል። ታሪኳ ጴጥሮስ (ሃዋሳ ከተማ)፣ ምትኬ ብርሃኑ (ሲዳማ ቡና)፣ ቤዛዊት ንጉሴ (መቻል) ፣ ህዳት ካሱ (ኢትዮ ኤሌክትሪክ)፣ ሊዲያ ኢያሱ (ጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ)፣ እና ማርያማዊት ታጠቅ (ኢትዮጵያ ስፖርት) በአጥቂ መስመር የሚገኙ ተጫዋቾች ናቸው። የኢትዮጵያ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ልምምዱን ከዛሬ ጀምሮ እንደሚያደርግ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር የሚያካሂደው የ’UEFA Frendship Cup’ ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ውድድር በቱርክዬ አስተናጋጅነት ከመጋቢት 28 እስከ ሚያዚያ 10 ቀን 2018 ዓ.ም ይከናወናል። በዚህ ውድድር ላይ ከተለያዩ አህጉራት የተውጣጡ ሀገራት የሚሳተፉ ሲሆን የኢትየጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ጋር በፈጠረው ግንኙነት ከአፍሪካ ከሚሳተፉ ሁለት ሀገራት መካከል አንዱ መሆን ችሏል። በዚህም ከ18 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ይሳተፋል። በዚህ ውድድር ላይ አስተናጋጇ ቱርክዬን ጨምሮ ኢትዮጵያ፣ ኖርዌይ፣ ኡዝቤኪስታን፣ ኮስታሪካ፣ ፓራጓይ፣ ዩራጓይ እና ሞሮኮ ተሳታፊ እንደሚሆኑ የተረጋገጡ ቡድኖች ናቸው
ይርጋጨፌ ቡና ከ12 ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት ተመልሷል
Mar 26, 2026 58
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ይርጋጨፌ ቡና አዲስ አበባ ከተማን 4 ለ 2 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ መንደሪን ክንድይሁን ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር አዳነች አስፋው እና ፍጹም ብርሃኑ ቀሪዎቹን ጎሎች ለይርጋጨፌ ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። አለሚ በዬቻ እና መሰረት ምክረ ለአዲስ አበባ ከተማ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ሁለት ግቦችን ያስቆጠረችው መንደሪን ክንድይሁን የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከ12 ጨዋታዎች በኋላ ወደ ድል የተመለሰው ይርጋጨፌ ቡና በ14 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ ሶስተኛ ድሉንም አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 16ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አዲስ አበባ ከተማ በ11 ነጥብ 13ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዝግጅቱን ጀመረ
Mar 26, 2026 61
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን በሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ከደቡብ ሱዳን ጋር ለሚያደርጋቸው የመጀመርያ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች ዛሬ ልምምድ ማድረግ ጀምሯል። ማለዳ ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተደረገው ልምምድ በአሰልጣኝ ራውዳ ዓሊ ጥሪ ከተደረገላቸው 23 ተጫዋቾች መካከል 16ቱ መገኘታቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። ቀሪዎቹ ተጫዋቾች ከዛሬ የክለብ ጨዋታዎች በኃላ ተጠቃለው ወደ ስብስቡ እንደሚገቡም አመልክቷል። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። ኢትዮጵያ የመጀመሪያ ዙር ማጣሪያ ጨዋታዋን በሚያዚያ ወር 2018 ዓ.ም ከደቡብ ሱዳን ጋር ታደርጋለች።
ወደ ዓለም ዋንጫ የሚያልፉ ቀሪ ስድስት ሀገራት የሚለዩባቸው የማጣሪያ ጨዋታዎች
Mar 26, 2026 128
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ 23ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ በአሜሪካ፣ ሜክሲኮ እና ካናዳ ጣምራ አዘጋጅነት ከሰኔ 4 እስከ ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። በዓለም ዋንጫው 48 ሀገራት የሚሳተፉ ሲሆን፤ እስከ አሁን 42 ሀገራት የተሳትፎ ትኬታቸውን ቆርጠዋል። በውድድሩ ላይ የሚሳተፉ ቀሪ ስድስት ሀገራት የሚለዩባቸው የመጀመሪያ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች ዛሬ ይካሄዳሉ። የዓለም ዋንጫ የአውሮፓ ጥሎ ማለፍ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ይከናወናሉ። ምሽት 2 ሰዓት ላይ ቱርክዬ ከሮማንያ በቱፕራስ ስታዲየም ይጫወታሉ። የአራት ጊዜ የዓለም ዋንጫ አሸናፊዋ ጣልያን ከሰሜን አየርላንድ፣ ዴንማርክ ከሰሜን ሜቄዶኒያ፣ ፖላንድ ከአልባኒያ፣ ቼክ ሪፐብሊክ ከአየርላንድ፣ ዩክሬን ከስዊድን፣ ስሎቫኪያ ከኮሶቮ እና ዌልስ ከቦሲኒያ እና ሄርዞጌቪና በተመሳሳይ ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ45 ላይ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የዛሬውን ጨዋታ የሚያሸንፉ ሀገራት ለዓለም ዋንጫው ለማለፍ ወደሚደረገው የመጨረሻ ማጣሪያ ያልፋሉ። በመጨረሻው ማጣሪያ የጣልያን እና ሰሜን አየርላንድ አሸናፊ ከዌልስ እና ቦሲኒያና ሄርዜጎቪና አሸናፊ፣ የፖላንድ እና አልባኒያ አሸናፊ ከዩክሬንና ስዊድን አሸናፊ፣ የቱርክዬና ሮማኒያ አሸናፊ ከስሎቫኪያና ኮሶቮ አሸናፊ እንዲሁም የዴንማርክ እና ሰሜን ሜቄዶኒያ አሸናፊ ከቼክ ሪፐብሊክ እና አየርላንድ አሸናፊ ጋር ይጫወታሉ። የመጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጨዋታዎችን የሚያሸንፉ አራት ሀገራት ለዓለም ዋንጫ ማለፋቸውን ያረጋግጣሉ። አራቱ ሀገራት አስቀድመው በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ያለፉ 12 የአውሮፓ ሀገራትን ይቀላቀላሉ። በዘንድሮው የዓለም ዋንጫ ከአውሮፓ 16 ሀገራት ይሳተፋሉ። በተያያዘም የክፍለ አህጉራት የዓለም ዋንጫ የጥሎ ማለፍ የመጀመሪያ ጨዋታዎችም ይካሄዳሉ። በማጣሪያው ላይ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ (አፍሪካ)፣ ኢራቅ (እስያ)፣ ቦሊቪያ (ደቡብ አሜሪካ)፣ ሱሪናም (ሰሜን/ማዕከላዊ አሜሪካ እና ካሪቢያን)፣ ጃማካይ (ሰሜን/ማዕከላዊ አሜሪካ እና ካሪቢያን) እና ኒው ካሌዶኒያ (ኦሽንያ) ይሳተፋሉ። በፊፋ የሀገራት የእግር ኳስ ደረጃ የተሻለ ደረጃ ያላቸው ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ (48ኛ) እና ኢራቅ (55ኛ) በቀጥታ ወደ መጨረሻው የማጣሪያ ጨዋታ አልፈዋል። ቀሪዎቹ አራት ሀገራት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታቸውን በሜክሲኮ ያደርጋሉ። ቦሊቪያ ከሱሪናም ከሌሊቱ 7 ሰዓት በስታዲዩ ቢቢቪኤ፣ ኒው ካሌዶኒያ ከጃማይካ በአክሮን ስታዲየም ከጠዋቱ 12 ላይ ይጫወታሉ። የኒው ካሌዶኒያ እና ጃማይካ አሸናፊ ከዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ የቦሊቪያ እና ሱሪናም አሸናፊ ከኢራቅ ጋር ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የመጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታቸውን ያሸነፉ ሁለት ሀገራት ለዓለም ዋንጫው ያልፋሉ።
የመውረድ ስጋት ያለባቸው ክለቦች የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
Mar 26, 2026 99
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ይርጋጨፌ ቡና ከአዲስ አበባ ከተማ በአበባ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ይርጋጨፌ ቡና በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በሁለቱ አሸንፎ በ13ቱ ተሸንፎ በአምስቱ አቻ ወጥቷል። በ20ዎቹ ጨዋታዎች ዘጠኝ ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 31 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አዲስ አዳጊው ይርጋጨፌ ቡና በ11 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው አዲስ አበባ ከተማ በሊጉ 20 ጨዋታዎች አከናውኖ ሶስት ጊዜ ድል ሲቀናው፤ በ15ቱ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 12 ግቦችን ሲያስቆጥር 41 ጎሎችን አስተናግዷል። አዲስ አበባ ከተማ በተመሳሳይ 11 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ 13ኛ ደረጃን በመያዝ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ይርጋጨፌ ቡና ባለፉት 12 የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በአንጻሩ አዲስ አበባ ከተማ ካሸነፈ ከወራጅ ቀጠና ይወጣል። በሌላኛው መርሐ-ግብር ድሬዳዋ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ድሬዳዋ ከተማ እስከ አሁን በሊጉ ማሸነፍ የቻለው ጨዋታ ብዛት ስድስት ነው። 11 ጊዜ ሲሸነፍ ሶስት ጊዜ አቻ ወጥቷል። 18 ግቦችን ሲያስቆጥር 31 ጎሎችን አስተናግዷል። ቡድኑ በ21 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ተጋጣሚው አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ 20 ጨዋታዎችን አድርጎ ሁለት ጊዜ ሲያሸንፍ፤ 14 ጊዜ ተሸንፏል። በአራት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 10 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 37 ጎሎች ተቆጥረውበታል። አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 14ኛ ደረጃን ይዟል። ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት አምስት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። አርባምንጭ ከተማ ባለፉት 13 ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ሁለቱም ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ ላለመውረድ በሚደረገው ፉክክር ወሳኝ የሚባሉ ናቸው። ቦሌ ክፍለ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ቦሌ ክፍለ ከተማ በ31 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ባህር ዳር ከተማ በ16 ነጥብ 10ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ቦሌ ክፍለ ከተማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ባህር ዳር ከተማ ካሸነፈ ሶስተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
Mar 25, 2026 86
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ኢትዮ ኤሌክትሪክ ሲዳማ ቡናን 2 ለ 0 አሸንፏል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ህዳት ካሡ ግቦቹን አስቆጥራለች። ግቦቹን ያስቆጠረችው ህዳት ካሡ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ከሁለት የአቻ ውጤቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ54 ነጥብ ከመሪው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር በነጥብ እኩል በመሆን በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ ሶስት ነጥብ አግኝቷል። በሊጉ 17ኛ ድሉንም አስመዝግቧል። የሁለቱ ቡድኖች በነጥብ እኩል መሆን የዋንጫ ፉክክሩን የበለጠ ሳቢ አድርጎታል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ ዘጠነኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ማሸነፍ አልቻለም። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ ጨዋታ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመቻል ጋር አንድ አቻ ተለያይቷል።
አዲስ አበባን ጽዱ፣ ውብና አረንጓዴ በማድረግ ለወጣቶች ምቹ የልማት ማዕከል የመገንባት ራዕይ በተግባር እየተረጋገጠ ነው
Mar 25, 2026 74
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ አዲስ አበባን ጽዱ፣ ውብና አረንጓዴ በማድረግ ለወጣቶች ምቹ የመዝናኛና የልማት ማዕከል የመገንባት ሥራ በተግባር እየተረጋገጠ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ በአራዳ ፓርክ የወጣቶች የኪነ-ጥበብ እና የፈጠራ ስራዎች የቀረቡበት መርሀ-ግብር አካሂዷል፡፡ የቢሮው ኃላፊ አቶ አሰግደው ኃይለጊዮርጊስ በዚሁ ወቅት፤ ከተማ አስተዳደሩ ወጣቶችን ታሳቢ ያደረጉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ማቀድ ብቻ ሳይሆን በተግባር በመፈጸም ውጤታማነቱን እያሳየ ይገኛል። በወንዝ ዳርቻና በኮሪደር ልማት የተገነቡ የወጣት ማዕከላት የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትልቅ ሚና በመጫወት ላይ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ በአራዳ ፓርክ የተካሄደው ወጣቶች የተሳተፉበት የባህላዊ ውዝዋዜ፣ የኪነ ጥበብ እና የፈጠራ ስራዎች መርሃ-ግብር ለዚህ ስኬት አብነት መሆኑን ጠቅሰዋል። እነዚህ ስፍራዎች ወጣቶች አብሮነታቸውንና ወንድማማችነታቸውን የሚያጠናክሩባቸው የጋራ መድረኮች ሆነው እያገለገሉ ይገኛሉም ብለዋል። መሰል የማዘውተሪያ ስፍራዎች ወጣቶች በሀገራቸው ላይ ትልቅ ተስፋ እንዲሰንቁና የፈጠራ አቅማቸውን ወደ ላቀ ደረጃ እንዲያሸጋግሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክቱ አስረድተዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ደጋፊዎች ማህበር ፕሬዝዳንት ምንያህል ጌታቸው እንዳለውም፣ አዲስ አበባ እንደ ስሟ እያበበች መሆኗን ገልጿል። የተገነቡት ማራኪ የመዝናኛ ስፍራዎች መንግስት ለወጣቱ ትውልድ የሚሰጠውን ልዩ ትኩረት የሚያሳዩና ተጠቃሚነትን በተጨባጭ ያረጋገጡ ስኬቶች መሆናቸውን ተናግሯል። ወጣት አርሴማ ሽመልስ በበኩሏ ቀደም ባሉት ጊዜያት በከተማዋ በቂ የወጣቶች መዝናኛ ስፍራዎች እንዳልነበሩ አስታውሳ አሁን የተገነቡት ስፍራዎች ለዓይን ማራኪ ከመሆናቸው ባለፈ፣ ወጣቶች ተሰጧቸውን የሚያሳዩበት ሰፊ ዕድል ፈጥሯል ብላለች፡፡
የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነጥብ ጣለ
Mar 25, 2026 81
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት ተጠባቂ መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና መቻል አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ንግሥት በቀለ በ66ኛው ደቂቃ ባስቆጠረችው ጎል ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሪ ሆኗል። ጨዋታው በንግድ ባንክ አሸናፊነት ተጠናቀቀ ሲባል ቱሪስት ለማ በ91ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ባሳረፈችው ግብ መቻል ወሳኝ አንድ ነጥብ አግኝቷል። ለመቻል ግቡን ያስቆጠረችው ቱሪስት ለማ የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ውጤቱን ተከትሎ የሊጉ መሪ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ነጥቡን ወደ 54 ከፍ አድርጓል። ከተከታዩ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት የማስፋት እድል አልተጠቀመበትም። መቻል በ45 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ በሊጉ አምስተኛ ተከታታይ ድሉን የማስመዝገብ ሙከራው አልተሳካም።
የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት ተጠባቂ ጨዋታዎች
Mar 25, 2026 92
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 21ኛ ሳምንት ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከረፋዱ አራት ሠዓት ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከመቻል በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሊጉ ባደረጋቸው 20 ጨዋታዎች በ17ቱ ድል ሲቀናው አንድ ጊዜ ተሸንፏል። በቀሪ ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በጨዋታዎቹ ላይ 58 ግቦችን ሲያስቆጥር ሰባት ግቦችን አስተናግዷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ንግድ ባንክ በ53 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው መቻል በሊጉ እስከ አሁን 20 ጨዋታዎች አከናውኖ 13 ጊዜ ሲያሸንፍ፤ በሁለቱ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች ነጥብ ጥሏል። 37 ጎሎችን ከመረብ ላይ ሲያገናኝ 11 ግቦች ተቆጥረውበታል። መቻል በ44 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካሸነፈ መሪነቱን ያጠናክራል። መቻል ካሸነፈ በሊጉ አራተኛ ተከታታይ ድሉን ያስመዘግባል። በ20ኛ ሳምንት ከቦሌ ክፍለ ከተማ በተደረገው ጨዋታ በቀይ ካርድ የወጣችው የመቻል አጥቂ ሴናፍ ዋቁማ በዛሬው ጨዋታ አትሰለፍም። ሁለቱ ቡድኖች በጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። ቡድኖቹ በመጀመሪያው ዙር ባደረጉት የሊጉ ጨዋታ ያለ ግብ አቻ መለያየታቸው የሚታወስ ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከሲዳማ ቡና ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ20 የሊጉ ጨዋታዎች በ16ቱ ሲያሸንፍ አንድ ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በ20ዎቹ ጨዋታዎች ላይ 44 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 11 ግቦች ተቆጥረውበታል። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ51 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ሲዳማ ቡና በውድድር ዓመቱ 20 ጨዋታዎች አድርጎ ስምንት ጊዜ ሲያሸንፍ፤ በተመሳሳይ በስምንት ጨዋታዎች ሽንፈት አጋጥሞታል። በቀሪ አራት ጨዋታዎች ነጥብ ተጋርቷል። 20 ግቦችን ከመረብ ጋር ሲያገናኝ 25 ጎሎችን አስተናግዷል። ሲዳማ ቡና በ28 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ የወጣው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ ማግኘት ለቡድኑ የዋንጫ ፉክክር ወሳኝ ነው። በ20ኛ ሳምንት ከድሬዳዋ ከተማ ጋር አንድ አቻ የተለያየው ሲዳማ ቡና ማሸነፍ ወደ ድል መንገድ ይመልሰዋል። የዛሬ ጨዋታዎች በዋንጫ ፉክክሩ ወሳኝ የሚባሉ ናቸው።
መሐመድ ሳላህ ሊቨርፑልን በዓመቱ መጨረሻ ይለቃል
Mar 25, 2026 141
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፦ የሊቨርፑሉ ኮከብ መሐመድ ሳላህ በውድድር ዓመቱ መጨረሻ ክለቡን እንደሚለቅ በይፋ አስታወቀ። ሳላህ ይህን ውሳኔውን ያሳወቀው ለደጋፊዎቹ ባስተላለፈው የቪዲዮ መልዕክት ነው። "ይህ ቀን በመምጣቱ አዝናለሁ... በውድድር ዓመቱ መጨረሻ ሊቨርፑልን እለቃለሁ። ይህ ክለብ፣ ይህች ከተማ እና ደጋፊዎቹ በህይወቴ ውስጥ ምን ያህል ትልቅ ቦታ እንዳላችሁ መግለጽ ይከብደኛል" ብሏል። የሊቨርፑል ክለብ ባወጣው መግለጫ ሳላህ የዘጠኝ ዓመት የክለብ ቆይታውን በሰኔ 2026 (እ.ኤ.አ) እንደሚያበቃ አስታውቋል። ተጫዋቹ ለደጋፊዎቹ ግልጽነት ለመፍጠር ሲል ውሳኔውን አሁን ለማሳወቅ መምረጡን ቢቢሲ ዘግቧል። ባለፉት ወራት በሳላህ እና በአሰልጣኝ አርኔ ስሎት መካከል የነበረው ግንኙነት መሻከር እና የተጫዋቹ የመሰለፍ ዕድል መቀነስ ለዚህ ውሳኔ በምክንያትነት ይጠቀሳሉ። ክለቡ እና ተጫዋቹ በጋራ ስምምነት ለመለያየት ወስነዋል። ሳላህ ምንም እንኳን የቀጣይ ክለቡ በይፋ ባይታወቅም፤ የሳዑዲ ዓረቢያ ክለቦች (በተለይም አል-ኢትሀድ) ተጫዋቹን ለመውሰድ ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸውና ድርድር ላይ እንደሆኑ በስፋት እየተዘገበ ይገኛል። የ33 ዓመቱ ሳላህ በሊቨርፑል 435 ጨዋታዎችን አድርጎ 255 ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ይህም ከኢያን ራሽ (346 ጎሎች) እና ከሮጀር ሀንት (285 ጎሎች) በመቀጠል በሊቨርፑል የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ዝርዝር ውስጥ በሶስተኝነት ደረጃ ላይ እንዲቀመጥ አድርጎታል።
የኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ መርሐ ግብር በሚያዝያ ወር ይካሄዳል
Mar 24, 2026 234
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ዋንጫ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ከሚያዝያ 14 እስከ 17 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄዱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታወቀ። በዚሁ መሰረት ቦዲቲ ከተማ ከመቀሌ 70 እንደርታ፣ ቤንች ማጂ ቡና ከኢትዮጵያ መድን፣ መቻል ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ነገሌ አርሲ ከሲዳማ ቡና ይጫወታሉ። ጨዋታዎቹ በአዲስ አበባ ስታዲየም እንደሚደረጉ ፌዴሬሽኑ ገልጿል።
ሃዋሳ ከተማ እና ሸገር ከተማ ነጥብ ተጋሩ
Mar 24, 2026 101
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ21ኛ ሳምንት መርሐ-ግብር ሃዋሳ ከተማ እና ሸገር ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ጨዋታው የተካሄደው በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ነው። የሸገር ከተማዋ ወርቅነሽ ዘሪሁን የጨዋታው ኮከብ ሆና ተመርጣለች። ሃዋሳ ከተማ በ43 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ሸገር ከተማ በ40 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ የ21ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ልደታ ክፍለ ከተማ አዳማ ከተማን 4 ለ 1 አሸንፏል።