ቀጥታ፡
ስፖርት
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና ወሳኝ ድል ተቀዳጅቷል
May 21, 2026 206
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና አርባምንጭ ከተማን 3 ለ 0 አሸንፏል። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ መስፍን ታፈሰ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር የአርባምንጭ ከተማው ኤፍሬም ታምራት በራሱ ላይ ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። በ14 ጎሎች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የሚመራው የሲዳማ ቡናው አጥቂ አቤል ያለው ባጋጠመው ጉዳት ምክንያት ወደ ህክምና ስፍራ ተወስዷል። ከአራት ጨዋታዎች በኋላ ወደ አሸናፊነት የተመለሰው ሲዳማ ቡና በ58 ነጥብ መሪነቱን አጠናክሯል። ከተከታዩ መቻል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ አድርጓል። በሊጉም 16ኛ ድሉን አስመዝግቧል። በአንጻሩ በውድድር ዓመቱ 14ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ በ29 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር አዳማ ከተማ እና ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ውጤቱን ተከትሎ አዳማ ከተማ በ39 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ድል አልቀናውም። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ40 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ33ኛ ሳምንት የመጨረሻ መርሐ ግብር ነገሌ አርሲ ከምድረ ገነት ሽሬ ምሽት 12 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ።
የሊጉ መሪ ሲዳማ ቡና በሊጉ ግርጌ ከሚገኘው አርባምንጭ ከተማ ጋር ይጫወታል
May 21, 2026 296
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ዛሬ ይጠናቀቃል። ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ አርባምንጭ ከተማ ከሲዳማ ቡና በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። አርባምንጭ ከተማ በ29 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃ ይዟል። ሲዳማ ቡና በ55 ነጥብ አንደኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት ሁለት የሊግ ጨዋታዎች ያላሸነፈው አርባምንጭ ከተማ ማሸነፍ በሊጉ የመቆየት ተስፋውን ለማለምለም የሚያስችለውን ሶስት ነጥብ እንዲያገኝ ያደርገዋል። ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ላይ ከድል የራቀው ሲዳማ ቡና ዛሬ ካሸነፈ ከተከታዩ መቻል ጋር ያለውን የነጥብ ልዩነት ወደ አምስት ከፍ ያደርጋል። ጨዋታው ለሁለቱም ቡድኖች ወሳኝ የሚባል ነው። በሌላኛው መርሐ ግብር ነገሌ አርሲ ከምድረ ገነት ሽሬ ምሽት 12 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ነገሌ አርሲ በ51 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ምድረ ገነት ሽሬ በ36 ነጥብ 17ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ32ኛ ሳምንት በመቻል የ4 ለ 0 ሽንፈት ያስተናገደው ነገሌ አርሲ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ እና በዋንጫ ፉክክሩ ለመቆየት ሶስት ነጥብ ማግኘት ይኖርበታል። በተመሳሳይ በ32ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ቡናን 1 ለ 0 ያሸነፈው ምድረ ገነት ሽሬ በዛሬው ጨዋታ ድል ከቀናው ከወራጅ ቀጠና ሊወጣበት የሚችልበት እድል ሊፈጠር ይችላል። ጨዋታው ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። አዳማ ከተማ ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። አዳማ ከተማ በ38 ነጥብ 16ኛ ደረጃን ይዟል። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ39 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። በ32ኛ ሳምንት መርሐ ግብር አዳማ ከተማ በፋሲል ከነማ የ3 ለ 1 ሽንፈት ሲያስተናግድ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 ረቷል። ጨዋታው ለሁለቱም ቡድኖች ከወራጅ ቀጠና ስፍራ ፈቀቅ ለማለት ወሳኝ የሚባል ነው። የዛሬ መርሐ ግብሮች ዋንጫ ለማንሳት እና ላለመውረድ በሚደረገው ፉክክር ላይ ተጽእኖ የሚያሳድሩ ናቸው።
አስቶንቪላ የዩሮፓ ሊግ ዋንጫን አነሳ
May 21, 2026 324
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በዩሮፓ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ አስቶንቪላ ፍራይበርግን 3 ለ 0 አሸንፏል። ማምሻውን በቱርኪዬ ኢስታንቡል በሚገኘው ቲውፕራሽ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዩሪ ቲሊማንስ፣ ኢሚሊያኖ ቡንዲያ እና ሞርጋን ሮጀርስ የማሸነፊያ ጎሎቹን አሳርፈዋል። በጨዋታው አስቶንቪላ የተሻለ ብልጫ የወሰደ ሲሆን ተጨማሪ ጎሎችን የማስቆጠር እድሎችን መጠቀም አልቻለም። የአስቶንቪላ ደጋፊ የሆኑት የዌልስ ልዑል ዊሊያምስ ጨዋታውን በስታዲየም በመገኘት ተከታትለዋል። ውጤቱን ተከትሎ አስቶንቪላ የዘንድሮው የዩሮፓ ሊግ አሸናፊ ሆኗል። ቪላ እ.አ.አ በ1982 የዩሮፓ ካፕ (የአሁኑ ሻምፒዮንስ ሊግ) ካነሳ 44 ዓመታት በኋላ ሌላኛውን የአውሮፓ ክብር ተቀዳጅቷል። ቡድኑ እ.አ.አ በ1996 የሊግ ካፕ ዋንጫውን ካነሳ በኋላ የመጀመሪያ ዋንጫውን አሳክቷል። ስፔናዊው የአስቶንቪላ አሰልጣኝ ኡናይ ኤምሬ ከተለያዩ ክለቦች ጋር ዩሮፓ ሊግ ዋንጫን አምስት ጊዜ በማንሳት አዲስ ታሪክ ጽፈዋል። ኤምሬ "የዩሮፓ ሊግ ንጉስ" የሚል የክብር ስም ተሰጥቷቸዋል። የዩሮፓ ሊግ አሸናፊው አስቶንቪላ በሊጉ አምስተኛ ደረጃን ይዞ ካጠናቀቀ በቀጣዩ ዓመት በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የሚሳተፉ የእንግሊዝ ክለቦች ብዛት ወደ ስድስት ያድጋል። ፍራይበርግ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ዋንጫ የማንሳት ህልሙ ሳይሳካ ቀርቷል።
ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ድሬዳዋ ከተማ ነጥብ ተጋሩ
May 20, 2026 303
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ እና ድሬዳዋ ከተማ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ማምሻውን በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሩዋንዳዊው ፓትሪክ ሲቦማና በ16ኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል ኢትዮ ኤሌክትሪክ መሪ ሆኗል። አስቻለው ታመነ በ63ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ድሬዳዋ ከተማን አቻ ያደረገውን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ46 ነጥብ ከነበረበት ስድስተኛ ደረጃ ወደ አራተኛ ከፍ ብሏል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አላሸነፈም። ድሬዳዋ ከተማ በ35 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሰባት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ዛሬ ቀን ላይ በተደረጉ የ33ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና ፋሲል ከነማን 2 ለ 1 ሲረታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሃዋሳ ከተማን፣ መቀሌ 70 እንደርታ ሸገር ከተማን በተመሳሳይ 1 ለ 0 አሸንፈዋል።
ሶስተኛው ዙር የክለቦች ቦክስ ሻምፒዮና መካሄድ ጀመረ
May 20, 2026 185
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ቦክስ ፌዴሬሽን የተዘጋጀው ሶስተኛው ዙር የክለቦች ቦክስ ሻምፒዮና በራስ ኃይሉ ስፖርትና ስልጠና ማዕከል ዛሬ መካሄድ ጀምሯል። በውድድሩ ላይ በሁለቱም ጾታዎች ከ12 ክለቦች የተወጣጡ 126 ቦክሰኞች ተሳታፊ ሆነዋል። ሻምፒዮናው ለስፖርተኞች ተከታታይነት ያለው የውድድር እድልን ለማመቻቸት፣​ በብሔራዊ ደረጃ ሀገርን ወክለው የሚወዳደሩ ብቁ ስፖርተኞችን ለመመልመልና ለመምረጥ ዓላማ ያደረገ ነው። በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት በሃገሪቱ መነቃቃት እየታየበት ላለው የካራቴ፣ ማርሻል አርት እና ኤምኤምኤ (MMA) ስፖርት ዘርፎች፤ ብቁ ስፖርተኞችን ከሻምፒዮናው በመመልመል ተጠቃሚ ማድረጉ የውድድሩ ሌላኛው ግብ ነው። የሶስተኛው ዙር የክለቦች ቦክስ ሻምፒዮና ውድድር ለአንድ ሳምንት እንደሚቆይ የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ሻምፒዮናው በዓመት አራት ጊዜ የሚካሄድ ነው። ሁለት ሻምፒዮናዎች አስቀድመው በአዲስ አበባ ተደርገዋል። የመጨረሻው ውድድር ከአንድ ወር በኋላ ይከናወናል። የአራቱ ውድድሮች አጠቃላይ ውጤት ተደምሮ በሁለቱም ጾታዎች አጠቃላይ አሸናፊ ክለቦች ይለያሉ።
ታሪካዊው የዩሮፓ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ- ፍራይቡርግ ከ አስቶንቪላ በኢስታንቡል
May 20, 2026 213
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12 /2018 (ኢዜአ)፦ በዩሮፓ ሊግ ፍራይቡርግ ከአስቶንቪላ ዋንጫውን ለማንሳት ዛሬ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በቱርኪዬ ኢስታንቡል ከተማ በሚገኘው ቲውፕራሽ ስታዲየም ይካሄዳል። በግማሽ ፍጻሜው አስቶንቪላ ኖቲንግሃም ፎረስትን በድምር ውጤት 4 ለ 1 በመርታት ለፍጻሜው ቀርቧል። አስቶንቪላ ከ44 ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ አውሮፓ መድረክ ፍጻሜ ተመልሷል። ፍራይቡርግ ከፖርቱጋሉ ብራጋ ጋር በነበረው ፍልሚያ በመጀመሪያው ጨዋታ 2 ለ 1 ተሸንፎ የነበረ ቢሆንም፣ ምሽት በሜዳው 3 ለ 1 በማሸነፍ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ለአውሮፓ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ ማለፉን አረጋግጧል። በኡናይ ኤምሬ የሚመራው አስቶን ቪላ እ.ኤ.አ በ1982 የአውሮፓ ካፕ (የአሁኑ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ) ያነሳ ባለታሪክ ክለብ ነው። አሰልጣኝ ኤምሬ በውድድሩ ላይ ለስድስተኛ ጊዜ ለፍጻሜ በመድረስ እና አራት ጊዜ ዋንጫ ማንሳታቸውን ተከትሎ "የአውሮፓ ሊግ ንጉስ" የሚል የክብር ስም ተሰጥቷቸዋል። አሰልጣኙ አምስተኛ ዋንጫቸውን በማንሳት አዲስ ታሪክ ለመጻፍ ሲዘጋጁ፣ በአንጻሩ ፍራይቡርግ በታሪኩ ምንም አይነት ትልቅ ዋንጫ አሸንፎ የማያውቅ በመሆኑ ይህ ጨዋታ ክለቡ ለመጀመሪያ ጊዜ በታሪኩ ትልቅ ስኬት እንዲያስመዘግብ የሚያስችለው ታሪካዊ አጋጣሚ ሆኖለታል። በፍራይቡርግ በኩል ተከላካዩ ሉካስ ኩብለር በግማሽ ፍጻሜው ያስቆጠራቸው ሁለት ወሳኝ ግቦች ለቡድኑ ስኬት ትልቅ ሚና ተጫውተዋል። በተጫዋቾች በኩል የሁለቱም ቡድኖች ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪዎች ለዋንጫው ወሳኝ ተጽዕኖ ያሳድራሉ ተብሎ ይጠበቃል። ከፍራይቡርግ በኩል አምስት ግቦችን ያስቆጠረው ጣሊያናዊው ቪንቼንዞ ግሪፎ እና አራት ግቦችን ከመረብ ያሳረፈው ጃፓናዊው ዩይቶ ሱዙኪ ቁልፍ ተጫዋቾች ናቸው። ከአስቶንቪላ በኩል አምስት ግቦችን ያስቆጠረው ኦሊ ዋትኪንስ እና በግማሽ ፍጻሜው ሁለት ግቦችን በማስቆጠር ድሉን ያረጋገጠው ካፒቴኑ ጆን ማክጊን የቡድኑ ዋና የማጥቃት ምንጮች ናቸው። ጨዋታው በሁለቱ ቡድኖች መካከል የሚደረግ የመጀመሪያው ግንኙነት ነው። በ36ኛ ሳምንት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሊቨርፑልን 4 ለ 2 ያሸነፈው አስቶንቪላ ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ማለፉን አረጋግጧል። አስቶንቪላ የዩሮፓ ሊግ ዋንጫን ካነሰ እና በሊጉ አምስተኛ ሆኖ ካጠናቀቀ በቀጣዩ የውድድር ዓመት ስድስት ክለቦች በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ይሳተፋሉ። የ37 ዓመቱ ፍራንስዋ ሌቲክሲየር የፍጻሜውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። የዩሮፓ ሊግ ከአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ በመቀጠል ሁለተኛ አህጉራዊ የክለቦች ውድድር ነው።
ኢትዮጵያ ቡና ከፋሲል ከነማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሃዋሳ ከተማ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ይጠበቃሉ
May 20, 2026 147
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ አራት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ኢትዮጵያ ቡና ከፋሲል ከነማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ቡና በ43 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ፋሲል ከነማ በ46 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት አራት ጨዋታዎች ከድል የራቁት ቡናማዎቹ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። በ32ኛ ሳምንት አዳማ ከተማን 3 ለ 1 የረታው ፋሲል ከነማ በድል ጉዞው ለመቀጠል ወደ ሜዳ ይገባል። በአዲስ አበባ ስታዲየም ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ የሚደረገው መርሐ ግብር ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ሃዋሳ ከተማን ያገናኛል። ቅዱስ ጊዮርጊስ በ40 ነጥብ 14ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሃዋሳ ከተማ በ45 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። የ16 ጊዜ የሊጉ አሸናፊ ቅዱስ ጊዮርጊስ በ32ኛ ሳምንት ከወላይታ ድቻ ጋር አቻ ከወጣበት ውጤት በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና አከባቢ ፈቀቅ እንዲል ያደርገዋል። ባለፉት ዘጠኝ የሊግ ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ የአሸናፊነቱን መንገድ ለማግኘት ይፋለማል። ኢትዮጵያ ቡና ከፋሲል ከነማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሃዋሳ ከተማ የሚያደርጓቸው ጨዋታዎች ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግባቸዋል ተብሎ ይጠበቃል። ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ ሸገር ከተማ ከመቀሌ 70 እንደርታ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሸገር ከተማ በ40 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው መቀሌ 70 እንደርታ በበኩሉ በ31 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ32ኛ ሳምንት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የ2 ለ 1 ሽንፈት ያስተናገደው ሸገር ከተማ ሶስት ነጥብ ለማግኘት ይጫወታል። ባለፉት አራት ጨዋታዎች ያላሸነፈው መቀሌ 70 እንደርታ ማሸነፍ ወደ ድል ከመመለስ ባለፈ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ፉክክር ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል። በዕለቱ የመጨረሻ መርሐ ግብር ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከድሬዳዋ ከተማ ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ45 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በ34 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። በ32ኛ ሳምንት በወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ 2 ለ 1 የተሸነፈው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ማሸነፍ ከወራጅ ቀጠና ለመውጣት በሚያደርገው ትግል ወሳኝ ሶስት ነጥብ ያስገኝለታል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ወደ ዓለም ዋንጫው የጥሎ ማለፍ ማጣሪያ አለፈች
May 20, 2026 151
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦‎ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ ቱኒዚያን 1 ለ 0 አሸንፏል። ትናንት ማምሻውን በመሐመድ ስድስተኛ ስፖርት ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አሚር ሚስባህ በ93ኛው ደቂቃ የማሸነፊያውን ጎል አስቆጥሯል። ጨዋታው ጠንካራ ፉክክር ተደርጎበታል። የኢትዮጵያ አምበል ቢኒያም አብርሃ የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተመርጧል። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ በምድብ አንድ አራት ነጥብ በመያዝ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ያጠናቀቀች ሲሆን ለዓለም ዋንጫ ወደ ሚያሳልፈው የማጣሪያ ጨዋታ አልፋለች። በዓለም ዋንጫው የመሳተፍ ተስፋዋም ቀጥሏል። ቱኒዚያ በአንድ ነጥብ አራተኛ ደረጃን በመያዝ ከውድድሩ ተሰናብታለች። በዚሁ ምድብ ማምሻውን በተካሄደ ጨዋታ አዘጋጇ ሞሮኮ ግብጽን 2 ለ 1 በማሸነፍ በሰባት ነጥብ የምድቡ መሪ ሆና በማጠናቀቅ ለሩብ ፍጻሜው ያለፈች ሲሆን ለዓለም ዋንጫ ማለፏንም አረጋግጣለች። ግብጽ በአራት ነጥብ ኢትዮጵያን በግብ ክፍያ በልጣ ሁለተኛ ደረጃን በመያዝ ወደ ዓለም ዋንጫው አልፋለች። 16 ሀገራት እየተሳተፉበት በሚገኘው የአፍሪካ ዋንጫ በአራቱ ምድብ አንደኛ እና ሁለተኛ የወጡ ስምንት ሀገራት ቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫው ያልፋሉ። ከየምድቡ ሶስተኛ የወጡ አራት ሀገራት ደግሞ በሚያደርጉት የጥሎ ማለፍ ማጣሪያ ቀሪ ሁለት አላፊ ቡድኖች ይለያሉ። ኢትዮጵያ በጥሎ ማለፉ ማጣሪያ መንገድ ወደ ዓለም ዋንጫ ለመግባት ትፋለማለች። የአፍሪካ ዋንጫው እስከ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በአፍሪካ ዋንጫው ከሚሳተፉ 16 ሀገራት መካከል የተሻለ ውጤት የሚያስመዘግቡ 10 ሀገራት በጥቅምት እና ህዳር ወር 2019 ዓ.ም በኳታር ለሚካሄደው 20ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ያልፋሉ። በዓለም ዋንጫው 48 ሀገራት ይሳተፋሉ።
አርሰናል ከ22 ዓመት በኋላ የፕሪሚየር ሊጉ ሻምፒዮን መሆኑን አረጋገጠ
May 20, 2026 149
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፦‎ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ቦርንማውዝ እና ማንችስተር ሲቲ አንድ አቻ ተለያይተዋል። ትናንት ማምሻውን በቫይታሊቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ጁኒየር ክሩፒ በ38ኛው ደቂቃ የቦርንማውዝን ጎል አስቆጥሯል። አርሊንግ ሃላንድ በ95ኛው ደቂቃ ሲቲን አቻ አድርጓል። ጨዋታው ተመጣጣኝ እና አዝናኝ ፉክክር ተደርጎበታል። ማንችስተር ሲቲ አቻ መውጣቱን ተከትሎ አርሰናል በ82 ነጥብ አንድ ጨዋታ እየቀረው ከ22 ዓመት በኋላ የሊጉ አሸናፊ መሆኑን አረጋግጧል። የአርሰናል የ22 ዓመት የሊጉ የዋንጫ ጥበቃትናንት ማምሻውን አብቅቷል። በሊጉ ስድስተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ማንችስተር ሲቲ በ78 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። በውድድር ዓመቱ 14ኛ ድሉን ያስመዘገበው ቦርንማውዝ በ56 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቦርንማውዝ ባለፉት 17 የሊግ ጨዋታዎች ባለመሸነፍ ድንቅ ግስጋሴ ላይ ይገኛል። የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ እሁድ ግንቦት 16 ቀን 2018 ዓ.ም በ38ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ይጠናቀቃል።
መቻል የሊጉ መሪ መሆን የሚችልበትን እድል ሳይጠቀምበት ቀረ
May 19, 2026 260
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ33ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ባህር ዳር ከተማ እና መቻል አንድ አቻ ተለያይተዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ አንተነህ ተፈራ በአራተኛው ደቂቃ ያስቆጠራት ጎል ባህር ዳር ከተማን መሪ አድርጓል። ፈቱዲን ጀማል በ82ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ ያሳረፈው ጎል መቻልን አቻ አድርጓል። ውጤቱን ተከትሎ መቻል በ53 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ከሲዳማ ቡና የሊጉን መሪነት መረከብ የሚችልበትን እድል አልተቀመበትም። ባህር ዳር ከተማ በ45 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ ሲሆን፣ ዘንድሮው በርካታ የአቻ ውጤት (18) ያስመዘገበ ቡድን ነው። በአዲስ አበባ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ሀዲያ ሆሳዕና እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ከሁለት ተከታታይ የሊግ ድሎች በኋላ አቻ የወጣው ሀዲያ ሆሳዕና በ42 ነጥብ 12ኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተመሳሳይ 42 ነጥብ በግብ ክፍያ በልጦ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ የ33ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ መድን እና ወላይታ ድቻ ያለ ግብ አቻ በመውጣት ነጥብ ተጋርተዋል።
የመዲናዋ የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ ልማቶች ለስፖርት ቱሪዝም እድገት ገንቢ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው
May 19, 2026 184
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በመዲናዋ የተገነቡ የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ ልማቶች ለስፖርት ቱሪዝም እድገት ገንቢ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽን ገለጸ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቱሪዝም ኮሚሽን "የስፖርት ቱሪዝም ለከተማችንና ለሀገራችን ያለው ፋይዳ" በሚል መሪ ሀሳብ ከባለድርሻ አካላት ጋር የፓናል ውይይት አካሒዷል። የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር ቢኒያም ታዬ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በመዲናዋ በርካታ የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎችን መሰረተ ልማቶች ተገንብተዋል፡፡ የስፖርት ማዘውተሪያ ሥፍራዎችና መሰረተ ልማቶች ለስፖርቱ ዘርፍ እድገት ገንቢ አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የስፖርት ቱሪዝም በዓለም አቀፍ ደረጃ ፈጣን እድገት እያሳዩ ካሉ ዘርፎች አንዱ መሆኑን ጠቅሰው፤ አዲስ አበባ ያሏትን መሰረተ-ልማት በመጠቀም ከዘርፉ የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በመዲናዋ በርካታ ደረጃዎችን የጠበቁ የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ ልማቶችና የቱሪዝም መዳረሻዎች ተገንብተው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውንም ገልጸዋል፡፡   የስፖርት ማዘውተሪያ መሰረተ-ልማቶቹ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ስፖርታዊ ውድድሮች እየተካሔዱባቸው መሆኑን ገልጸው፤ እነዚህ ሁነቶቹ ለመዲናዋ የስፖርት ቱሪዝም እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከቱሪዝም ዘርፍ ማግኘት ያለባት ጥቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ እንዲመጣ አስተዋጽኦ ማድረጉንም ገልጸዋል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ የማህበረሰብ አቀፍ ስፖርት ማስፋፊያና ተሳትፎ ዳይሬክተር እንግዳወርቅ ዳንኤል በበኩላቸው፤ በመዲናዋ የተገነቡና እየተገነቡ ያሉ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ከተማዋን የዓለም አቀፍና አህጉራዊ የስፖርት ማዕከል እንድትሆን አድርጓታል ብለዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቱሪዝም ልማትና ማኔጅመንት ተባባሪ ፕሮፌሰር ሽፈራው ሙለታ (ዶ/ር)፤ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት የስፖርት ቱሪዝም ዕድገት እንዲነቃቃ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ የስፖርት መሰረተ ልማቶች ከተማዋን ውብ እና ጽዱ ከማድረግ ባሻገር ለስፖርት ቱሪዝም ማደግ ከፍተኛ ድርሻ አበርክተዋል ያሉት ደግሞ የሆቴል ዘርፍ አሰልጠኝና አማካሪው ሰለሞን ታዬ ናቸው፡፡
የዓለም ዋንጫ ተስፋን ለማለምለም የሚደረግ ፍልሚያ፤ ቀይ ቀበሮዎች ከካርቴጅ ንስሮች
May 19, 2026 234
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በ16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ የመጨረሻ ጨዋታዋን ዛሬ ከቱኒዚያ ጋር ታከናውናለች። ጨዋታው ምሽት አራት ሰዓት ላይ በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ አካዳሚ ይካሄዳል። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመራው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በምድብ አንድ ባደረጋቸው ሁለት ጨዋታዎች አንድ ጊዜ ሲሸነፍ በቀሪው መርሐ ግብር አቻ ተለያይቷል። ከግብጽ ጋር ያለ ግብ አቻ ሲለያይ በአዘጋጇ ሞሮኮ 2 ለ 1 ተሸንፏል። ብሔራዊ ቡድን በአንድ ነጥብ አራተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ቡድኑ ከሞሮኮ ጋር በነበረው ጨዋታ የተሻለ እንቅስቃሴ አድርጓል። ተጋጣሚዋ ቱኒዚያ ከሁለት ጨዋታዎች አንድ ነጥብ በማግኘት ሶስተኛ ደረጃን ይዟል። ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ዓለም ዋንጫ የማለፍ ህልሟን ለማለምለም የግድ ቱኒዚያን ማሸነፍ ይጠበቅበታል። ቀይ ቀበሮቹ ሁለተኛ ደረጃን ይዘው ካጠናቀቁ ቀጥታ በኳታር ለሚካሄደው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በቀጥታ ያልፋሉ። በአንጻሩ ሶስተኛ ከወጡ ወደ ዓለም ዋንጫ ለማለፍ ወደ ሚደረገው ማጣሪያ ይሸጋገራሉ። አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር ከጨዋታው በፊት በሰጡት አስተያየት አላማቸውን ለዓለም ዋንጫ ማለፍ መሆኑን ተናግረዋል። ለዚህም እየሰራን ነው ሲሉ ገልጸዋል። ብሔራዊ ቡድኑ እስከ መጨረሻው እንደሚፋለም እና ቱኒዚያን ለማሸነፍ እንደሚጫወት ተናግረዋል። ቡድኑ ከጨዋታው በፊት የመጨረሻ ልምምዱን ትናንት በመሐመድ ስድስተኛ አካዳሚ ማከናወኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። በዚሁ ምድብ በተመሳሳይ ከምሽቱ አራት ሰዓት አዘጋጇ ሞሮኮ ከግብጽ ጋር ትጫወታለች። ሞሮኮ እና ግብጽ በተመሳሳይ አራት ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ይዘዋል። ጨዋታው በአቻ ውጤት ከተጠናቀቀ ሁለቱ ሀገራት በቀጥታ ወደ ዓለም ዋንጫ ማለፋቸውን ያረጋግጣሉ። ጨዋታውን የሚያሸንፈው ቡድን ለዓለም ዋንጫ ከማለፍ ባለፈ ምድቡን በመሪነት ያጠናቅቃል። ሽንፈት የሚያስተናግደው ብሔራዊ ቡድን በሂሳባዊ ስሌት ወደ ዓለም ዋንጫው የመግባት እድል አለው። 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ እስከ ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። በአፍሪካ ዋንጫው ከሚሳተፉ 16 ሀገራት መካከል የተሻለ ውጤት የሚያስመዘግቡ 10 ሀገራት በጥቅምት እና ህዳር ወር 2019 ዓ.ም በኳታር ለሚካሄደው 20ኛው የፊፋ ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ያልፋሉ። በዓለም ዋንጫው 48 ሀገራት ይሳተፋሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም