ቀጥታ፡
ስፖርት
ኢትዮጵያ በ20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር በሁለቱም ጾታዎች የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 16, 2026 54
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛ የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ዛሬ አምስተኛ ቀኑን ይዟል። በወንዶች 20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር አትሌት ምስጋናው ዋቁማ አሸንፏል። ውድድሩን በአንደኝነት በማጠናቀቅ በአፍሪካ ሻምፒዮና መድረክ በተከታታይ ለሁለተኛ ጊዜ በማሸነፍ ክብሩን አስጠብቋል። ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት አብዱልሰላም አብዱልዋሂብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ የነሐስ ሜዳሊያ ለሀገሩ አስገኝቷል።   በሴቶች 20 ኪሎ ሜትር የርምጃ ውድድር ደግሞ አትሌት ውብአለም ሽጉጤ በቀዳሚነት አጠናቃ የወርቅ ሜዳሊያ አግኝታለች። በዚሁ ውድድር ላይ የተካፈሉት አትሌት ሕይወት አምባው አራተኛ እንዲሁም አትሌት ማሬ ቢተው ስምንተኛ ደረጃን በመያዝ ውድድራቸውን አጠናቀዋል። ውጤቶቹን ተከትሎ ኢትዮጵያ ያገኘቻቸው የወርቅ ሜዳሊያዎች ብዛት አምስት ደርሰዋል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው አምስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና አምስት የነሐስ በድምሩ 11 ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። ሻምፒዮናው ነገ ይጠናቀቃል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ዛሬ ይጠናቀቃል
May 16, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ይጫወታሉ። ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ36 ነጥብ 16ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ተጋጣሚው ኢትዮ ኤሌክትሪክ በ45 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ማግኘት ያልቻለው ወልዋሎ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታል። ሶስት ነጥብ ከወራጅ ቀጠና ስፍራ ፈቀቅ እንዲል ያደርገዋል። በ31ኛ ሳምንት ፋሲል ከነማን 3 ለ 1 የረታው ኢትዮ ኤሌክትሪክ ካሸነፈ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል። ሃዋሳ ከተማ ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ባለፉት ስምንት ጨዋታዎች ከድል የራቀው ሃዋሳ ከተማ በ44 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። አርባምንጭ ከተማ በ28 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ በ31ኛ ሳምንት በወላይታ ድቻ የ3 ለ 2 ሽንፈት አስተናግዷል። ሃዋሳ ከተማ ከድል ጋር ለመታረቅ፣ አርባምንጭ ከተማ ላለመውረድ በሚያደርገው ትግል ሶስት ነጥብ ለማግኘት የሚያደርጉት ፍልሚያ ትኩረትን ስቧል። ምሽት 12 ሰዓት ላይ ፋሲል ከነማ ከአዳማ ከተማ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ፋሲል ከነማ በ43 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ይዟል። አዳማ ከተማ በ38 ነጥብ 15ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባለፉት አራት የሊግ ጨዋታዎች ድል ያልቀናው ፋሲል ከነማ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ወደ ሜዳ ይገባል። በ31ኛ ሳምንት ምድረ ገነት ሽሬን 4 ለ 0 በመርታት ከስምንት ጨዋታዎች በኋላ ሶስት ነጥብ ያገኘው አዳማ ከተማ ተከታታይ ድሉን ለማስመዝገብ ይጫወታል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን የሞሮኮ አቻውን ይገጥማል
May 16, 2026 80
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በሞሮኮ አስተናጋጅነት የሚካሄደው 16ኛው ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ዛሬ አራተኛ ቀኑን ይዟል። በምድብ አንድ የሚገኘው የኢትዮጵያ ታዳጊ ብሔራዊ ቡድን ሁለተኛ ጨዋታውን ዛሬ ከአዘጋጇ ሞሮኮ ጋር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ ኮምፕሌክስ ያደርጋል። ብሔራዊ ቡድኑ በመጀመሪያ ጨዋታው ከግብጽ ጋር ያለ ግብ አቻ በመውጣት አንድ ነጥብ አግኝቷል። ቡድኑ በጨዋታው ላይ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ አድርጓል። አዘጋጇ ሞሮኮ በመጀመሪያ ጨዋታ ቱኒዚያን 3 ለ 0 በማሸነፍ ምድቡን እየመራች ነው። በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ቤንጃሚን ዚመር የሚመዋር ቡድን ከምድቡ ለማለፍ እና በኳታር ለሚደረገው ከ17 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ የማለፍ ህልሙን ለማሳካት ከዛሬው ጨዋታ ሶስት ነጥብ ማግኘት ይጠበቅበታል። የአጥቂ መስመሩ የሚፈጠሩ የግብ ዕድሎችን ወደ ውጤት የመቀየር አቅሙን ማሳደግ ይኖርበታል። ብሔራዊ ቡድኑ ከጨዋታው በፊት የመጨረሻ ልምምዱን በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ አካዳሚ ማድረጉንና ሁሉም ተጫዋቾች በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የሁለቱ ሀገራት ጨዋታ ጠንካራ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። በዚሁ ምድብ ከቀኑ 10 ሰአት ላይ ቱኒዚያ ከግብጽ በመሐመድ ስድስተኛ እግር ኳስ ኮምፕሌክስ ይጫወታሉ።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊጉ የ25ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን መርሐ ግብር
May 16, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ዛሬ ሁለት ጨዋታዎች ይካሄዳሉ። ከጠዋቱ ሶስት ሰዓት ላይ አዳማ ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይጫወታሉ። ባለፉት ሰባት ጨዋታዎች ከድል የራቀው አዳማ ከተማ በ22 ነጥብ 10ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ድሬዳዋ ከተማ በ25 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ድሬዳዋ ከተማ ባለፉት አራት ተከታታይ የሊግ ጨዋታዎች አላሸነፈም። ሁለቱም ቡድኖች ዓመቱን አሸናፊነት ለማጠናቀቅ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ሸገር ከተማ ከይርጋጨፌ ቡና ከረፋዱ አምስት ላይ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሸገር ከተማ በ47 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ይርጋጨፌ ቡና በ18 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ26ኛ ሳምንት በቦሌ ክፍለ ከተማ 2 ለ 0 የተሸነፈው ሸገር ከተማ ዓመቱን በድል ለመቋጨት ይፋለማል። ይርጋጨፌ ቡና ካሸነፈ ወይም አቻ ከወጣ በሊጉ መቆየቱን ያረጋግጣል።
የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ማን ያነሳል? ቼልሲ ወይስ ማንችስተር ሲቲ?
May 16, 2026 115
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ ቼልሲ እና ማንችስተር ሲቲ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ለማንሳት ዛሬ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ጨዋታው ከቀኑ 11 ሰዓት ላይ 90 ሺህ ተመልካች በሚያስተናግደው ዌምብሌይ ስታዲየም ይካሄዳል። ቼልሲ ሊድስ ዩናይትድን እንዲሁም ማንችስተር ሲቲ ሳውዝሃምተንን በማሸነፍ ለፍጻሜው ማለፋቸው የሚታወስ ነው። ሁለቱ ክለቦች በኤፍኤ ካፕ ታሪካቸው ለ10ኛ ጊዜ የሚገናኙ ሲሆን፣ ቀደም ባሉት ዘጠኝ ግንኙነቶች ማንችስተር ሲቲ ስድስት ጊዜ በማሸነፍ የበላይነቱን ይዟል። በአንጻሩ ቼልሲ በቀሪዎቹ ሶስት ጨዋታዎች ድል ቀንቶታል። በዘጠኙ ጨዋታዎች ላይ ማንችስተር ሲቲ 16 ግቦችን ሲያስቆጥር ቼልሲ ዘጠኝ ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቡድኖቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በውድድሩ ላይ የተገናኙት እ.አ.አ በ1915 በሶስተኛ ዙር ላይ ሲሆን ቼልሲ 1 ለ 0 አሸንፏል። እ.አ.አ በ2024 ለመጨረሻ ጊዜ በተገናኙበት የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ማንችስተር ሲቲ 1 ለ 0 በመርታት ለፍፃሜው አልፏል። ቼልሲ ለኤፍኤ ካፕ ፍጻሜ ሲያልፍ ይህ ለ17ኛ ጊዜው ነው። የምዕራብ ለንደኑ ክለብ እስከ አሁን ስምንት ጊዜ የዋንጫው ባለቤት መሆን ችሏል። ማንችስተር ሲቲ ለ14ኛ ጊዜ ለፍጻሜ የደረሰ ሲሆን፣ እስካሁን ባደረጋቸው የፍጻሜ ጨዋታዎች ሰባት ጊዜ ዋንጫውን አንስቷል። ሁለቱ ቡድኖች ታሪካዊውን ዋንጫ ለማንሳት የሚያደርጉት ፍልሚያ ፣ ብርቱ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ ይጠበቃል። ቼልሲ የኤፍኤ ካፕ ዋንጫን ካነሳ ለዩሮፓ ሊግ ማለፉን ያረጋግጣል። የ40 ዓመቱ ዳረን ኢንግላንድ ተጠባቂውን ጨዋታ በዋና ዳኝነት ይመሩታል። 154 ዓመታትን ያስቆጠረው ኤፍኤ ካፕ የዓለማችን እጅግ አንጋፋው የእግር ኳስ ውድድርነው።
አስቶንቪላ ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ማለፉን አረጋገጠ
May 16, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የ37ኛ ሳምንት የመጀመሪያ መርሐ ግብር አስቶንቪላ ሊቨርፑልን 4 ለ 2 ረቷል። በቪላ ፓርክ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ኦሊ ዋትኪንስ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር ሞርጋን ሮጀርስ እና ጆን ማጊን ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።   ቨርጅል ቫን ዳይክ ለሊቨርፑል ጎሎቹን አስቆጥሯል። በሊቨርፑሉ አማካይ ዶምኒክ ስቦዝላይ በተሰራው ስህተት ኦሊ ዋትኪንስ ያስቆጠረው ጎል የጨዋታው ቁልፍ ክስተት ነበር። ሊቨርፑል በጨዋታው የሰራቸው ስህተቶች ዋጋ አስከፍሎታል። ጨዋታው አዝናኝ እንቅስቃሴ የተደረገበት ሲሆን አስቶንቪላ ግልጽ የግብ እድሎችን በተሻለ ሁኔታ ፈጥሯል። በሊጉ 18ኛ ድሉን ያስመዘገበው አስቶንቪላ በ62 ነጥብ አራተኛ ደረጃን በመያዝ አንድ ጨዋታ እየቀረው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎውን አረጋግጧል። በውድድር ዓመቱ 12ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሊቨርፑል በ59 ነጥብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ሊቨርፑል በሻምፒዮንስ ሊጉ ለመሳተፍ በ38ኛ ሳምንት ብሬንትፎርድን ማሸነፍ ይጠበቅበታል።
ባህር ዳር ከተማ እና ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ድል ቀንቷቸዋል
May 15, 2026 120
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተካሄደዋል። በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተደረገው ጨዋታ ባህር ዳር ከተማ ድሬዳዋ ከተማን 2 ለ 0 አሸንፏል። ፍፁም ፍትዓለው እና አንተነህ ተፈራ ግቦቹን አስቆጥረዋል። በሊጉ ዘጠነኛ ድሉን ያስመዘገበው ባህር ዳር ከተማ በ44 ነጥብ ደረጃውን ከ9ኛ ወደ 6ኛ ከፍ አድርጓል። በውድድር ዓመቱ 13ኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ድሬዳዋ ከተማ በ34 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ስድስት የሊግ ጨዋታዎች ከድል ርቋል። በአዲስ አበባ ስታዲየም የተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሸገር ከተማን 2 ለ 1 ረቷል። አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል ለንግድ ባንክ ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። ቢንያም ፍቅሩ የሸገር ከተማን የማስተዛዘኝ ግብ አስቆጥሯል። በውድድር ዓመቱ 10ኛ ድሉን ያገኘው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ41 ነጥብ ከነበረበት 14ኛ ደረጃ ወደ 11ኛ ከፍ ብሏል። በሊጉ ስምንተኛ ሽንፈቱን ያስተናገደው ሸገር ከተማ ደግሞ በ40 ነጥብ ከ12ኛ ደረጃ ወደ 13ኛ ወርዷል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ተጫዋቾቹ አዲስ ግደይ እና ናትናኤል ዳንኤል በሊጉ ያስቆጠሩትን የግብ መጠን በተመሳሳይ 11 በማድረስ፣ በ14 ግቦች የከፍተኛ ግብ አግቢነቱን ደረጃ እየመራ የሚገኘውን የሲዳማ ቡናውን አቤል ያለውን ይከተላሉ። ዛሬ አስቀድሞ በተደረገ የ32ኛ ሳምንት ጨዋታ መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ ተለያይተዋል።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ32ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ጨዋታዎች
May 15, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 32ኛ ሳምንት ዛሬ ሶስት ጨዋታዎች ይደረጋሉ። የዕለቱ ቀዳሚ መርሐ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ኢትዮጵያ መድንን ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ያገናኛል። መቀሌ 70 እንደርታ በ30 ነጥብ 19ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ቡድኑ ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች ከድል ርቋል። ኢትዮጵያ መድን በ40 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ባለፉት ሶስት የሊግ ጨዋታዎች አሸንፏል። ጨዋታው መቀሌ 70 እንደርታ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ኢትዮጵያ መድን በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው። ድሬዳዋ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ባለፉት አምስት የሊግ ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ያላገኘው ድሬዳዋ ከተማ በ34 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛሉ። ባህር ዳር ከተማ በ41 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት ከወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ጋር ያለ ግብ አቻ ተለያይቷል። ባህር ዳር ከተማ በዘንድሮው የውድድር ዓመት በርካታ የአቻ ውጤቶችን (17 ጊዜ) ያስመዘገበ ቡድን ነው። ሁለቱም ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ይጫወታሉ። በሌላኛው መርሐ ግብር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከሸገር ከተማ ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ይጫወታሉ። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ38 ነጥብ 14ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ሸገር ከተማ በ40 ነጥብ 12ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። በ31ኛ ሳምንት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኢትዮጵያ መድን የ2 ለ 1 ሽንፈት ሲያስተናግድ ሸገር ከተማ የሊጉን መሪ ሲዳማ ቡናን 1 ለ 0 አሸንፏል። ጨዋታው ንግድ ባንክ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ፣ ሸገር ከተማ በድል ጉዞው ለመቀጠል የሚያደርጉት ነው።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የማጠናቀቂያ ጨዋታዎች ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳሉ
May 15, 2026 122
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ የ25ኛ ሳምንት መርሐ ግብር የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሶስት ጨዋታዎች በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይደረጋሉ። ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ ልደታ ክፍለ ከተማ ከባህር ዳር ከተማ ይጫወታሉ። ልደታ ክፍለ ከተማ በ22 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ባህር ዳር ከተማ በ19 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። በ26ኛ ሳምንት ወራጁን አርባምንጭ ከተማን 4 ለ 1 ያሸነፈው ልደታ ክፍለ ከተማ ዓመቱን በድል ለመቋጨት ይጫወታል። በ26ኛ ሳምንት በአዲስ አበባ ከተማ 3 ለ 1 የተሸነፈው ባህር ዳር ከተማ ዓመቱን ድል ለማሳረግ ወደ ሜዳ ይገባል። በሌላኛው መርሐ ግብር ሲዳማ ቡና ከአርባምንጭ ከተማ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ያከናውናሉ። ሲዳማ ቡና በ35 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃን ይዟል። ወደ ሴቶች ከፍተኛ ሊግ መውረዱ የተረጋገጠው አርባምንጭ ከተማ በ10 ነጥብ የመጨረሻውን 20ኛ ደረጃን ይዟል። በ25ኛ ሳምንት ይርጋጨፌ ቡና ያለ ግብ አቻ የተለያየው ሲዳማ ቡና ዓመቱን በማሸነፍ ለመፈጸም ይጫወታል። ከፕሪሚየር ሊጉ ለወረደው አርባምንጭ ከተማ ጨዋታው ከመርሐ ግብር ማሟያነት የዘለለ ትርጉም የለውም። ሃዋሳ ከተማ ከቦሌ ክፍለ ከተማ ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። ሃዋሳ ከተማ በ49 ነጥብ አራተኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚው ቦሌ ክፍለ ከተማ በ43 ነጥብ ስድስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። ሁለቱ ቡድኖች ዓመቱን በድል ለማጠናቀቅ የሚያደርጉት ፍልሚያ ተመጣጣኝ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በ66 ነጥብ ሊጉን እየመራ ነው። ኢትዮ ኤሌክትሪክ በተመሳሳይ 66 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። የኢትዮ ኤሌክትሪኳ ዳግማዊት ሰሎሞን በ24 ግቦች የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራች ይገኛል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ረድኤት አስረሳኸኝ ደግሞ በ20 ግቦች ተከታዩን ስፍራ ይዛለች።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዝግጅት
May 14, 2026 234
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከብሩንዲ ጋር ለሚያደርገው ሁለተኛ ዙር የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታ የሁለተኛ ቀን ልምምዱን ዛሬ አድርጓል። አሰልጣኝ ራውዳ ዓሊ ለ30 ተጫዋቾች ጥሪ በማድረግ ትናንት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሜዳ ዝግጅታቸውን የጀመሩ ሲሆን ጥሪ የተደረገላቸው ተጫዋቾች ሁሉም ተገኝተው ልምምዳቸውን አከናውነዋል። በብሔራዊ ቡድኑ የሁለተኛ ቀን ዝግጅት ተጫዋቾች የእርስ በእርስ ጨዋታዎችን በማድረግ አቋማቸውን መፈተሻቸውን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከብሩንዲ ጋር ግንቦት 16 የመጀመሪያ ጨዋታውን በሜዳው፣ የመልስ ጨዋታውን ግንቦት 23 ቡጁምቡራ ላይ ያከናውናል። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። በማጣሪያ የሚያልፉ አራት የአፍሪካ ሀገራት በሶስት ዙሮች በሚደረጉ ጨዋታዎች ይለያሉ።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና ሶስተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አገኘች
May 14, 2026 172
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018 (ኢዜአ)፦ ሶስተኛ ቀኑን ባስቆጠረው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተለያዩ ውድድሮች በመካሄድ ላይ ናቸው። ማምሻውን በተደረገው የ3000 ሜትር መሰናክል የወንዶች የፍጻሜ ውድድር አትሌት ገመቹ ጎዳና 8 ደቂቃ ከ41 ሴኮንድ ከ02 ማይክሮ ሴኮንድ አንደኛ ወጥቷል። አትሌት ገመቹ ለኢትዮጵያ በሻምፒዮናው ሶስተኛውን የወርቅ ሜዳሊያ አስገኝቷል። በውድድሩ ላይ የተሳተፈው ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ሳሙኤል ፍሬው ሶስተኛ በመውጣት የነሐስ ሜዳሊያ ባለቤት ሆኗል። በ800 ሜትር ሴቶች ፍፃሜ አትሌት ምስጋና ኃይሉ እና በ400 ሜትር ሴቶች ፍጻሜ አትሌት አጃይባ አልዩ የወርቅ ሜዳሊያ ማግኘታቸው ይታወቃል። ኢትዮጵያ እስከ አሁን በሻምፒዮናው ሶስት የወርቅ፣ አንድ የብር እና ሶስት የነሐስ በድምሩ ሰባት ሜዳሊያዎችን አግኝታለች። በጋና አክራ እየተካሄደ የሚገኘው 24ኛው የአፍሪካ አትሌቲክስ ሻምፒዮና እስከ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም