ቀጥታ፡
ስፖርት
በዓለም አቀፍ ውድድሮች የቀጠለው የኢትዮጵያ አትሌቶች ድል
Jun 7, 2026 707
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 30/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በዓለም አቀፍ ውድድሮች ድል ማስመዝገባቸውን ቀጥለዋል። በብራዚል በተካሄደው የሪዮ ዴ ጃኔይሮ ማራቶን ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች ድል ሲቀዳጁ፣ በስቶኮልም ዳይመንድ ሊግ ደግሞ አትሌት ብርቄ ሓየሎም አሸናፊ ሆናለች። ዛሬ በተካሄደው የዘንድሮው የሪዮ ዴ ጃኔይሮ ማራቶን ውድድር፣ በሴቶች አትሌት ጋዲሴ ሙሉ 2 ሰዓት ከ25 ደቂቃ ከ46 ሴኮንድ አሸናፊ ሆናለች።   ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከ1ኛ እስከ 5ኛ ያለውን ደረጃ በአጠቃላይ በመቆጣጠር ፍጹም የበላይነታቸውን አሳይተዋል። አትሌት ትርፌ ፀጋዬ 2ኛ፣ አትሌት አዝመራ አብረሃ 3ኛ፣ አትሌት አፍራ ጉዳፈይ 4ኛ እና ዝናሽ ደበበ 5ኛ ደረጃን ይዘው ጨርሰዋል። በወንዶች አትሌት ፀጋዬ ጌታቸው በአስደናቂ አጨራረስ ውድድሩን በአንደኝነት አጠናቋል። ፀጋዬ ውድድሩን ለመጨረስ 2 ሰዓት ከ10 ደቂቃ ከ23 ሰከንድ የወሰደበት ሲሆን፣ ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት አንተንአየሁ ይስማ በሴኮንድ ልዩነት ተበልጦ ሁለተኛ መሆን ችሏል።   በሌላ በኩል በስዊድን ስቶኮልም በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ ውድድር አትሌት ብርቄ ሓየሎም በ1500 ሜትር አሸንፋለች። ብርቄ ከሁለት ቀናት በፊት በሩሲያ ሞስኮ በተካሄደው ተመሳሳይ የርቀት ውድድር በአንደኝነት ማጠናቀቋ የሚታወስ ሲሆን፣ አሁን ደግሞ በአጭር የሰዓታት ልዩነት 4:00.68 በስቶኮልም ዳግም በማሸነፍ አስደናቂ ብቃቷን አሳይታለች። በዚሁ ውድድር ላይ የተካፈለችው ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት አትሌት ሐረገወይኒ ካላዩ ውድድሩን አራተኛ ደረጃን ይዞ ማጠናቀቁን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል።
በ19ኛው የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶን ውድድር አትሌት ጌታቸው ማስረሻና አትሌት መሰለች አለማየሁ አሸነፉ
Jun 7, 2026 541
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 30/2018 (ኢዜአ)፦ 19ኛው የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶን ዛሬ ረፋድ ላይ መነሻ እና መድረሻውን መስቀል አደባባይ በማድረግ ተካሂዷል። በወንዶች ውድድር የሸገር ሲቲው አትሌት ጌታቸው ማስረሻ አንደኛ በመውጣት በድል አጠናቋል። ባየልኝ ተሻገር ከኢትዮ ኤሌክትሪክ ሁለተኛ፣ በላይ ጥላሁን ከአዲስ አበባ አትሌቲክስ ክለብ ሶስተኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል። በሴቶች የአዲስ አበባ ፖሊሷ መሰለች አለማየሁ አሸናፊ ሆናለች። ዝማም ባራኪ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ስታጠናቅቅ የሸገር ሲቲዋ በቀለች ተኩ ሶስተኛ ደረጃን ይዛ ጨርሳለች። በ19ኛው የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶን 455 እና በሴቶች 183 በድምሩ 638 አትሌቶች ተሳታፊ ሆነዋል። የውድድሩ ዋና አላማ በዴንማርክ ኮፐንሃገን በመስከረም ወር 2019 ዓ.ም ለሚካሄደው 26ኛው የዓለም አትሌቲክስ የግማሽ ማራቶን ሻምፒዮና ኢትዮጵያን የሚወክሉ አትሌቶች መምረጥ እና ተተኪዎችን ማፍራት ነው። በውድድሩ ላይ ከ1ኛ እስከ 6ኛ ደረጃ ይዘው ያጠናቀቁ አትሌቶች የገንዘብ፣ሜዳሊያና የዋንጫ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። የዘንድሮው ውድድር ተሳታፊዎች ብዛት ከአምናው ጋር ሲነጻጸር የ434 አትሌቶች ጭማሪ ማሳየቱን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል። #ኢዜአ #Ethiopian_News_Agency
በሮም እና ሞስኮ የደመቁት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች
Jun 6, 2026 985
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሮምና በሞስኮ በተካሄዱ ዓለም አቀፍ ውድድሮች ላይ ድል አስመዝግበዋል። የዘንድሮው የዝናሜንስኪ ሜሞሪያል አትሌቲክስ ውድድር የኢትዮጵያውያን አትሌቶች ደማቅ ድል የተመዘገበበት መድረክ ሆኗል። በሩሲያ ሞስኮ በተካሄደውና በዓለም አትሌቲክስ የ“F” ደረጃ በተሰጠው የ2026 የዝናሜንስኪ ወንድማማቾች መታሰቢያ የአትሌቲክስ ውድድር ላይ፣ የኢትዮጵያ አትሌቶች አስደናቂ ብቃት በማሳየት ውድድሩን በድል አጠናቀዋል። በሩሲያ ዋና ከተማ በተካሄደው በዚህ ውድድር ላይ በርካታ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች የተሳተፉ ሲሆን፥ በአራት የተለያዩ የርቀት ዓይነቶችም የወርቅ ሜዳሊያዎችን ማሸነፍ ችለዋል። በሴቶች የ1500 ሜትር ውድድር አትሌት ብርቄ ኃይሎም ርቀቱን በ3:58.59 በሆነ ፈጣን ሰዓት በማጠናቀቅ አንደኛ ወጥታለች። አትሌት ሳሮን በርሄ በ4:01.96 ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች። በዚሁ ውድድር ላይ አትሌት ደስታ ታደለ 5ኛ፣ አትሌት ሲፈን ዳገታ 8ኛ፣ አትሌት በሻቱ ጌታ 9ኛ፣ እንዲሁም አትሌት ቤተልሔም ሙላት 15ኛ ደረጃን ይዘው አጠናቀዋል። በሴቶች የ10000 ሜትር ውድድር አትሌት ፈንታዬ ጫኔ በ32:23.54 አንደኛ በመሆን ስታሸንፍ፣ አትሌት ቤተልሔም ኦላና በ32:25.57 ሁለተኛ ሆና አጠናቃለች። ሌሎቹ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ሰላማዊት ሻምበል 4ኛ እንዲሁም አትሌት ትርንጎ ታደለ 6ኛ ደረጃን በመያዝ ውድድራቸውን ፈጽመዋል። በሴቶች 3000 ሜትር መሰናክል ውድድር፣ ብርቱ ፉክክር በተደረገበት የሩጫ መድረክ አትሌት ብርቱካን ገዳሙ ርቀቱን በ9:36.20 በማጠናቀቅ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በሴቶች 800 ሜትር ውድድር አትሌት ሀብታም ገበየሁ በ2:02.53 በሆነ ሰዓት 6ኛ ደረጃን ይዛ አጠናቃለች። በወንዶች የ10,000 ሜትር ውድድር ላይ አትሌት እዮብ ስመኝ እጅግ ግሩም ውጤት አስመዝግቧል። አትሌት እዮብ ርቀቱን በ27:55.75 በማጠናቀቅ ውድድሩን በአሸናፊነት አጠናቋል። በዚሁ ውድድር ላይ ሌላኛው ኢትዮጵያዊ አትሌት ሽመልስ ንጉሴ በ28:16.57 ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ ማጠናቀቅ ችሏል። በወንዶች 3000 ሜትር መሰናክል ውድድር አትሌት ዲንቃ ፍቃዱ ርቀቱን በ8:35.32 አንደኛ በመሆን በበላይነት አሸንፏል። አትሌት ሂርኮ ኃይሉ በበኩሉ ርቀቱን በ8:38.24 በማጠናቀቅ ሶስተኛ ደረጃን ይዞ ጨርሷል። የ2026 ዳይመንድ ሊግ አራተኛ መዳረሻ በሆነው የሮሙ የሴቶች 5000 ሜትር ውድድር፣ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከአንደኛ እስከ ሰባተኛ ያለውን ደረጃ በሙሉ በመቆጣጠር በበላይነት አጠናቀዋል። በውድድሩም አትሌት ልቅና አምባው በ14:18.41 የወቅቱን የዓለም ፈጣን ሰዓት በማስመዝገብ የባለድልነት ዘውዱን ደፍታለች። አትሌት ልቅና አምባው የግሏን ምርጥ ሰዓት ከዓምስት ሰከንድ በላይ ማሻሻል የቻለች ሲሆን፥ የወቅቱ የርቀቱ ፈጣን በሆነው 14:18.41 ሰዓት ውድድሩን አሸንፋለች። ይህች አትሌት ቀደም ሲል በሻንጋይ ዳይመንድ ሊግ ውድድር ላይ ሁለተኛ ደረጃን ይዛ ማጠናቀቋ የሚታወስ ነው። በዚሁ የሮም ውድድር አትሌት አለሚቱ ባወቀ በ14:18.54 ሁለተኛ እንዲሁም አትሌት ፍሬወይኒ ኃይሉ በ14:18.94 ሶስተኛ በመሆን ውድድሩን ማጠናቀቃቸውን የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶን ውድድር ነገ በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Jun 6, 2026 599
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦ 19ኛው የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶን ውድድር ነገ ግንቦት 30 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይደረጋል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ውድድሩን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን ጋዜጣዊ ዛሬ መግለጫ ሰጥቷል። መነሻው እና መድረሻውን መስቀል አደባባይ ያደረገው ውድድር ላይ በወንዶች 455፣ በሴቶች ደግሞ 183 በድምሩ 638 አትሌቶች እንደሚሳተፉ በመግለጫው ላይ ተጠቁሟል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ኮማንደር አትሌት ስለሺ ስህን የውድድሩ ዋና አላማ በስዊድን ለሚካሄደው የግማሽ ማራቶን ውድድሩ ኢትዮጵያን የሚወክሉ አትሌቶች መምረጥ እና ተተኪዎች ማፍራት ነው ብለዋል። የፌዴሬሽኑ ውድድር እና ተሳትፎ ተወካይ ዳይሬክተር አቶ ጊዜ አድነው በበኩላቸው በውድድሩ ላይ ከ1ኛ እስከ 6ኛ ደረጃ ይዘው የሚያጠናቅቁ አትሌቶች የገንዘብ፣ የሜዳልያና የዋንጫ ሽልማት እንደሚበረከትላቸው አመልክተዋል። የዘንድሮው ውድድር ተሳታፊዎች ብዛት ከአምናው ጋር ሲነጻጸር የ434 አትሌቶች ጭማሪ ማሳየቱን የፌዴሬሽኑ መረጃ ያመለክታል።
ኢትዮጵያ ከማላዊ ጋር የወዳጅነት ጨዋታ ታደርጋለች
Jun 6, 2026 523
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከማላዊ አቻው ጋር ዛሬ ዓለም አቀፍ የወዳጅነት ጨዋታውን ያከናውናል። ጨዋታው ከምሽቱ 12 ሰዓት ላይ በድሬዳዋ ስታዲየም ይካሄዳል። አሰልጣኝ ዮሐንስ ሳህሌ ለወዳጅነት ጨዋታዎቹ ዝግጅት ግንቦት 19 ቀን 2018 ዓ.ም ለ23 ተጫዋቾች ያደረጉ ሲሆን፣ ብሔራዊ ቡድኑ ከግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ ዝግጅቱን በአዲስ አበባ እና ድሬዳዋ ሲያደርግ ቆይቷል። ዋልያዎቹ ዛሬ ከሚያደርጉት የመጀመሪያ ጨዋታ በፊት የመጨረሻ ልምምዳቸውን ትናንት በድሬዳዋ ስታዲየም አከናውኗል። ሁሉም የብሔራዊ ቡድኑ ተጫዋቾች በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል። የ55 ዓመቱ ዚምባቡዌያዊ አሰልጣኝ ካሊስቶ ፓሱዋ ለጨዋታው ለ23 ተጫዋቾች ጥሪ አድርገው ቡድኑ ዝግጅቱን ሲያደርግ ቆይቷል። ነበልባሎቹ የመጨረሻ ልምምዳቸውን ትናንት በድሬዳዋ ስታዲየም አድርጓል። ኢትዮጵያ እና ማላዊ ከዚህ ቀደም በውድድር እና በወዳጅነት ጨዋታዎች 14 ጊዜ ተገናኝተዋል። ዋልያዎቹ አራት ጊዜ ድል ሲቀናቸው ማላዊ አምስት ጊዜ አሸንፋለች። በቀሪ አምስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይተዋል። ኢትዮጵያ በጨዋታዎቹ ላይ 16 ግቦችን ከመረብ ላይ ስታሳርፍ ማላዊ 14 ጎሎችን አስቆጥራለች:: ሁለቱ ሀገራት ለመጨረሻ ጊዜ የተገናኙት እ.አ.አ በ2022 እና በ2023 በኮትዲቯር ለተካሄደው 34ኛ የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ባደረጉት የማጣሪያ ጨዋታ ነበር። ከሁለቱ የማጣሪያ ጨዋታዎች መካከል ማላዊ አንዱን ስታሸንፍ በቀሪው ጨዋታ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። ኢትዮጵያ ማላዊን ለመጨረሻ ጊዜ ያሸነፈችው እ.አ.አ በ2021 በባህር ዳር ስታዲየም በተካሄደ የወዳጅነት ጨዋታ ሲሆን ብሔራዊ ቡድኑ በወቅቱ የ4 ለ 0 ድል አስመዝግቧል። እ.አ.አ 1983 ቡድኖቹ ባደረጉት የመጀመሪያ ጨዋታ ማላዊ ኢትዮጵያን 4 ለ 0 አሸንፋለች። ጨዋታው፣ እ.አ.አ በ1986 በሜክሲኮ ለተስተናገደው 13ኛው የፊፋ ዓለም ዋንጫ የተደረገ የአፍሪካ ዞን ማጣሪያ ነበር። ሁለቱ ሀገራት ዛሬ ለ15ኛ ጊዜ ይገናኛሉ። በፊፋ የደረጃ ሰንጠረዥ ኢትዮጵያ 144ኛ፣ ማላዊ ደግሞ 127ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ብሔራዊ ቡድኖቹ ሁለተኛ የወዳጅነት ጨዋታቸውን ሰኔ 2 ቀን 2018 ዓ.ም በድሬዳዋ ስታዲየም ያደርጋሉ። ዋልያዎቹ ጨዋታዎቻቸውን የሚያደርጉት፣ የፊፋ ዓለም አቀፍ የብሔራዊ ቡድኖች የጨዋታ ቀናትን (FIFA Window) በመጠቀም መሆኑን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶን ውድድር በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Jun 5, 2026 454
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ)፦ 19ኛው የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶን ውድድር እሁድ ግንቦት 30 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይደረጋል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ውድድሩን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። መነሻው እና መድረሻውን መስቀል አደባባይ ያደረገው ውድድር ላይ በወንዶች 455፣ በሴቶች ደግሞ 183 በድምሩ 638 አትሌቶች እንደሚሳተፉ በመግለጫው ላይ ተጠቁሟል። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ኮማንደር አትሌት ስለሺ ስህን የውድድሩ ዋና አላማ በስዊድን ለሚካሄደው የግማሽ ማራቶን ውድድር ኢትዮጵያን የሚወክሉ አትሌቶች መምረጥ እና ተተኪዎች ማፍራት ነው ብለዋል። የፌዴሬሽኑ ውድድር እና ተሳትፎ ተወካይ ዳይሬክተር አቶ ጊዜ አድነው በበኩላቸው በውድድሩ ላይ ከ1ኛ እስከ 6ኛ ደረጃ ይዘው የሚያጠናቅቁ አትሌቶች የገንዘብ፣ሜዳልያና የዋንጫ ሽልማት እንደሚበረከትላቸው አመልክተዋል። የዘንድሮው ውድድር ተሳታፊዎች ብዛት ከአምናው ጋር ሲነጻጸር የ434 አትሌቶች ጭማሪ ማሳየቱን የፌዴሬሽኑ መረጃ ያመለክታል።
የረቀቁ የአበረታች ቅመሞች አጠቃቀም ስልቶችን ለመከላከል የሚያስችል ተቋማዊ አቅም እየተገነባ ነው-ባለስልጣኑ
Jun 4, 2026 696
አዳማ፤ ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ)፦ የረቀቁ የአበረታች ቅመሞች አጠቃቀም እና የማጭበርበር ስልቶችን ለመግታት የሚያስችል ተቋማዊ አቅም እየተገነባ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር መኮንን ይደርሳል ገለጹ። የኢትዮጵያ ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን በስፖርት ውስጥ የተከለከሉ አበረታች ቅመሞች (Doping) እና ዘዴዎች አስመልክቶ ለስፖርት ጋዜጠኞች ያዘጋጀው የስልጠናና የውይይት መድረክ በአዳማ እየተካሄደ ይገኛል።   መድረኩ ባለስልጣኑ የተከለከሉ አበረታች ቅመሞች (Doping) እና ዘዴዎች የሚፈጥሩትን አሉታዊ ተፅዕኖ የመከላከል እና የመቆጣጠር ስራ ይበልጥ ውጤታማ እና ተደራሽ ለማድረግ እያከናወነው ባለው ስራ የስፖርት ጋዜጠኞች ያላቸውን ሚና ማሳደግን ያለመ ነው። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር መኮንን ይደርሳል የስፖርት ጋዜጠኞች በአበረታች ቅመሞች ዙሪያ የስፖርት ማህረሰቡን እና የባለድርሻ አካላትን ግንዛቤ በመፍጠር ውጤታማ ስራዎችን መስራት እንደሚችሉ ገልጸዋል። የፀረ አበረታች ቅመሞች ስራ ከሚዲያ ስራ ነጥሎ ማየት እንደማይቻል ጠቅሰው፥ በዚህ ረገድም ሚዲያ የማይተካ ሚና እንዳለው አመልክተዋል። በአበረታች ቅመሞች ዙሪያ ባለፉት ዓመታት ሚዲያው ተግቶ ሲሰራ መቆየቱንና የአመላካከት ለውጥ እየመጣ መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ፀረ አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን ከነበረበት ችግር ወጥቶ ባለፉት ዓመታት ጠንካራ ተቋማዊ አቅም በመገንባት በአፍሪካ እና ዓለም አቀፍ ደረጃ ተምሳሌት መሆን መቻሉን ተናግረዋል። የፀረ አበረታች ቅመሞች ስራ የበለጠ በሳይንስ እና ቴክኖሎጂ እየታገዘ እንደሚገኝና ባለስልጣኑም ከወቅቱ ጋር በመራመድ ተቋማዊ ብቃቱንና የመፈጸም አቅሙን ለማሳደግ እየሰራ ነው ብለዋል። የአበረታች ቅመሞች በስርዓተ ትምህርት ውስጥ መካተትና በስፖርት እና የስልጠና ማዕከላት ተከታታይ ግንዛቤ መፍጠር ስራዎች እየተከናወኑ በመሆናቸው በዘላቂነት ውጤት እንደሚያመጡ ገልጸዋል። ባለስልጣኑ የምርምር እና የቁጥጥር አቅሙ መጨመሩን እያሳደገ እንደሚገኝና ህገ ወጥ ተግባር በሚፈጽሙ አትሌቶች እና ሌሎች አካላት ላይ የህግ እርምጃ እየተወሰደ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የምርምር እና ቁጥጥር ተሞክሮ እና ውጤቶች ማስፋት እና ማጠናከር እንደሚገባም ነው ዋና ዳይሬክተሩ የገለጹት። የፀረ አበረታች ቅመሞች የመከላከል እና የመቆጣጠር አቅም ማደግ የኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ ተሳትፎ፣ተወዳዳሪነት እና ውጤታማነት ለማሳደግ እንደሚያስችል አመልክተዋል። በዓለም አቀፍ ውድድሮች ተሳትፎን ለማረጋገጥ የፀረ አበረታች ቅመሞች መመዘኛዎች ማሟላት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። የስፖርት ፍትሃዊነት ማረጋገጥ እንደሚገባ ጠቅሰው፥ አትሌቶች ሙያ፣ ተፈጥሯዊ ጥረት እና አቅም በመጠቀም ውጤት ለማምጣት መስራት አለባቸው ብለዋል። የስፖርቱን ተአማኒነት ለማጽናት እና ለማስቀጠል የፀረ አበረታች ቅመሞች ስራ ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት አመልክተዋል። አትሌቶች እና ዜጎች ከጤና፣ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ሌሎች ችግሮችና ቀውሶች ለመጠበቅ የቁጥጥርና የምርመራ ስራውን ማጠናከር ተገቢ እንደሆነም አንስተዋል። የአበረታች ቅመሞች አጠቃቀም በቴክኖሎጂ እና ሳይንስ ታግዘው እየረቀቁ መምጣታቸውን የተናገሩት ዋና ዳይሬክተሩ ከጊዜው ጋር የሚሄድ ቀጣይነት ያለው ተቋማዊ አቅም ግንባታ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል። በዚህ ረገድም መገናኛ ብዙሃን የተከለከሉ አበረታች ቅመሞች መከላከል እና መቆጣጠር ላይ ያላቸውን ግንዛቤ መፍጠር እና የአመለካከት ለውጥ የማምጣት ስራ እንዲያጠናክሩ ጥሪ አቅርበዋል። በውይይቱ ላይ ዶፒንግ ፤ የጋዜጠኞች ስነ ምግባር፤ የአበረታች ቅመሞች ፅንሰ ሀሳቦች፣ ዓለም አቀፍ የዶፒንግ ተጽእኖና የኢትዮጵያ ፀረ አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን እንቅስቃሴ በሚሉ ጉዳዮች ላይ የመወያያ ሰነዶች ቀርበው ውይይት እንደሚደረግባቸው የወጣው መርሐ ግብር ያሳያል። የኢትዮጵያ ፀረ-አበረታች ቅመሞች ባለስልጣን በሀገራችን ስፖርት ውስጥ የተከለከሉ አበረታች ቅመሞች (Doping) እና ዘዴዎች የሚፈጥሩትን አሉታዊ ተፅዕኖ ለመከላከል እና ለመቆጣጠር በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 400/2009 ስልጣን ተሰጥቶት የተቋቋመ የፌዴራል ተቋም ሲሆን ባለፉት 8 ዓመታት በርካታ ስራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛል። ከእነዚህም መካከል ህብረተሰቡንና የስፖርቱን ቤተሰብ በስፋት ለማንቃት የተጠናከሩ የሚዲያ ንቅናቄ ፕሮግራሞችን በተለያዩ የሚዲያ ተቋማትና የማህበራዊ ትስስር ገጾች ላይ በስፋት ተግባራዊ ማድረግ ይገኝበታል።
የወላይታ ድቻ እና የነገሌ አርሲ የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር
Jun 4, 2026 626
  አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ)፦ በዝናብ ምክንያት የተራዘመው የወላይታ ድቻ እና የነገሌ አርሲ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት ጨዋታ ዛሬ ይካሄዳል። ጨዋታው ከቀኑ 9 ሰዓት በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ይከናወናል። ወላይታ ድቻ በሊጉ ካደረጋቸው 33 ጨዋታዎች መካከል በዘጠኙ ድል ሲቀናው ስምንት ጊዜ ሽንፈት አስተናግዷል። በቀሪ 16 ጨዋታዎች ላይ አቻ ተለያይቷል። በ33ቱ ጨዋታዎች ላይ 32 ግቦችን ከመረብ ላይ ሲያሳርፍ 29 ግቦችን አስተናግዷል። ወላይታ ድቻ በ43 ነጥብ 11ኛ ደረጃን ይዟል። ተጋጣሚ ነገሌ አርሲ በበኩሉ 33 ጨዋታዎችን አድርጎ በ13ቱ ሲያሸንፍ በሰባቱ ተሸንፏል። 13 ጊዜ ደግሞ ነጥብ ተጋርቷል። 32 ግቦችን ሲያስቆጥር 25 ጎሎች ተቆጥረውበታል። ነገሌ አርሲ በ52 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ይገኛል። ወላይታ ድቻ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ነገሌ አርሲም ካለፉት ሁለት ጨዋታዎች ሶስት ነጥብ ማግኘት አልቻለም። ጨዋታው ሁለቱ ቡድኖች ወደ አሸናፊነት ለመመለስ የሚያደርጉት ነው። ግንቦት 21 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ስታዲየም ሊካሄድ የነበረው የወላይታ ድቻ እና የነገሌ አርሲ ጨዋታ፣ በወቅቱ በጣለው ከባድ ዝናብ ምክንያት ወደ ዛሬ መዛወሩ ይታወሳል።
በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ በርካታ ጨዋታዎችን በማድረግ ክብረ ወሰን የያዘው ጀምስ ሚልነር ራሱን ከእግር ኳስ ተጫዋችነት አገለለ
Jun 1, 2026 827
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 24 /2018 (ኢዜአ)፦ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ታሪክ የምንጊዜም ከፍተኛውን የጨዋታ ተሳትፎ ክብረ ወሰን የያዘው ጀምስ ሚልነር፣ ከ24 ዓመታት የሊግ ቆይታ በኋላ በ40 ዓመቱ ከእግር ኳስ ተጫዋችነት ራሱን ማግለሉን አስታወቀ። የቀድሞው የእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድን ተጫዋች በረጅም የእግር ኳስ ዘመኑ ለሊድስ ዩናይትድ፣ ኒውካስል ዩናይትድ፣ አስቶንቪላ፣ ማንቸስተር ሲቲ፣ ሊቨርፑል እና ብራይተን ኤንድ ሆቭ አልቢዮን ተጫውቷል። ያለፉትን ሶስት የውድድር ዓመታት በብራይተን ያሳለፈው ሚልነር፣ የእግር ኳስ ዘመኑን የጀመረው በልጅነት ክለቡ ሊድስ ዩናይትድ ሲሆን እ.ኤ.አ. በ2002 ገና በ16 ዓመቱ በፕሪሚየር ሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን ማድረጉ ይታወሳል። ተጫዋቹ በአጠቃላይ 24 የውድድር ዘመናትን በሊጉ ያሳለፈ ሲሆን፣ ባለፈው የካቲት ወር ላይ ብራይተን ከብሬንትፎርድ ጋር ባደረገው ጨዋታ የሊጉን የምንጊዜም ከፍተኛ የመጫወት ክብረ ወሰን መስበር መቻሉ ይታወቃል። በሊጉ 658 ጨዋታዎችን ማድረጉን ስካይ ስፖርት ዘግቧል። ጀምስ ሚልነር የስንብት ውሳኔውን አስመልክቶ በሰጠው አስተያየት፥ በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ 24 የውድድር ዘመናትን ካሳለፍኩ በኋላ፥ አሁን ለተጫዋችነት ዘመኔ ማጠቃለያ ለመስጠት ትክክለኛው ጊዜ እንደሆነ ይሰማኛል ሲል ገልጿል። ሚልነር በልጅነቱ ለሚደግፈው ሊድስ ዩናይትድ በ16 ዓመቱ ተሰልፎ የሊጉ ትንሹ ጎል አስቆጣሪ በሆነበት ወቅት፤ በረጅም የእግር ኳስ ሕይወቱ እንዲህ ዓይነቱን አስደናቂ ታሪክ ይጽፋል ብሎ በፍጹም እንዳልገመተ ገልጿል። ባለፈው የውድድር ዓመት እግሩን ማንሳት እንኳ እስከማይችልበት ከባድ ጉዳት ደርሶበት የነበረ ቢሆንም፣ በድጋሚ አገግሞ በመመለስ በ40 ዓመቱ ብራይተን በታሪኩ ለሁለተኛ ጊዜ ለአውሮፓ መድረክ እንዲበቃ ማገዝ መቻሉን በደስታና በኩራት እንደሚመለከተው ተጫዋቹ አክሎ ገልጿል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ከዛምቢያ ጋር ይጫወታል
May 31, 2026 728
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ ኢትዮጵያ የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ ጨዋታዋን ከዛምቢያ ጋር ታደርጋለች። የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ትናንት በሁለተኛ ዙር የመልስ ጨዋታ ብሩንዲን 2 ለ 1 በማሸነፍ በድምሩ ተጋጣሚውን 4 ለ 2 በመርታት ለመጨረሻው ዙር ማጣሪያ አልፏል። በአሰልጣኝ ራውዳ አሊ የሚመራው ብሔራዊ ቡድን የመጨረሻ ዙር ጨዋታውን ከዛምቢያ ጋር እንደሚያደርግ ታውቋል። የዛምቢያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ዛሬ ከሜዳው ውጪ ባደረገው የመልስ ጨዋታ 2 ለ 0 አሸንፏል። በኪባሳ ማሊባ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ፒዳህ ሙዙዋ እና ኤልሳቤት ሞፍያ ግቦቹን አስቆጥረዋል። ውጤቱን ተከትሎ ዛምቢያ በድምር ውጤት 7 ለ 0 በማሸነፍ የመጨረሻውን ዙር ተቀላቅላለች። ዛምቢያ ከኢትዮጵያ ጋር ለዓለም ዋንጫው ለማለፍ ትጫወታለች። ኢትዮጵያ ከዛምቢያ ጋር የዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎቿን በሰኔ ወር መጨረሻ እና ሐምሌ ወር መጀመሪያ ላይ ታደርጋለች። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። ቀሪ አራት ሀገራት በማጣሪያ ጨዋታዎች ይለያሉ።
ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ የካራቴ ሻምፒዮና አራት የወርቅ ሜዳሊያዎችን አገኘች
May 31, 2026 465
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የካራቴ ሻምፒዮና ከግንቦት 20 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በኬንያ ናይሮቢ እየተካሄደ ይገኛል። በሻምፒዮና ላይ እየተሳተፈ የሚገኘው የኢትዮጵያ ካራቴ ብሔራዊ ቡድን እስከ አሁን ዘጠኝ ሜዳሊያዎችን አግኝቷል። ብሔራዊ ቡድኑ በወንዶች ከ75 ኪሎ ግራም በታች እና ከ53 ኪሎ ግራም በታች፣ እንዲሁም በሴቶች ካታ እና በቡድን የካራቴ ኩሚቴ አራት የወርቅ ሜዳሊያዎችን ማግኘት ችሏል። በተጨማሪም በወንዶች ከ67 ኪሎ ግራም በታች እና በቡድን ካታ ውድድር ሁለት የብር ሜዳሊያዎች ተገኝተዋል። በወንዶች ካታ፣ ከ60 ኪሎ ግራም በታች እና ከ84 ኪሎ ግራም በታች ሶስት የነሐስ ሜዳሊያዎች የተመዘገበባቸው ሌሎች ዘርፎች ናቸው። የምስራቅ አፍሪካ የካራቴ ሻምፒዮና ውድድር ዛሬ ፍጻሜውን የሚያገኝ ሲሆን አምስት አገራት መሳተፋቸውን የባህል እና ስፖርት ሚኒስቴር አስታውቋል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2025 በአዲስ አበባ በተካሄደው የምስራቅ አፍሪካ የካራቴ ሻምፒዮና አጠቃላይ አሸናፊ እንደነበረች የሚታወስ ነው።
ፒኤስጂ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫን ለተከታታይ ጊዜ አነሳ
May 30, 2026 1007
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የፍጻሜ ጨዋታ ፒኤስጂ አርሰናልን በመለያ ምት አሸንፏል። ማምሻውን በሀንጋሪ ቡዳፔስት በሚገኘው ፑሽካሽ አሬና ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ካይ ሃቫርትዝ በስድስተኛው ደቂቃ ባስቆጠረው ጎል አርሰናል መሪ ሆኗል። የፒኤስጂው አምበል ማርኪኒዮስ ስህተት ለሃቫርትዝ ግብ መቆጠር ምክንያት ሆኗል። ከእረፍት መልስ ኡስማን ዴምቤሌ በ65ኛው ደቂቃ በፍጹም ቅጣት ምት ከመረብ ላይ ባሳረፈው ጎል ፒኤስጂ አቻ መሆን ችሏል። የወቅቱ የባለንዶር አሸናፊ ዴምቤሌ ዘንድሮ በውድድሩ ላይ ያስቆጠራቸውን ጎሎች ብዛት ስምንት አድርሷል። መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአቻ ውጤት በመጠናቀቁ ምክንያት 30 ደቂቃ ተጨምሯል። በጭማሪ ሰዓት ግብ ባለመቆጠሩ ምክንያት ጨዋታው ወደ መለያ ምት አምርቷል። ፒኤስጂ በመለያ ምት 4 ለ 3 በማሸነፍ ለተከታታይ የውድድር ዓመት የሻምፒዮንስ ሊጉን ዋንጫ አንስቷል። የአውሮፓ ክብሩን አስጠብቋል። የፓሪሱ ክለብ ከሪያል ማድሪድ በኋላ ለተከታታይ ዓመት ዋንጫውን ያነሳ ቡድን ሆኗል። የሰሜን ለንደኑ ክለብ አርሰናል ለመጀመሪያ ጊዜ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የማንሳት ህልሙ አልተሳካም። አርሰናል ከፕሪሚየር ሊጉ ድል በኋላ ድርብ ስኬት ማሳካት አልቻለም።
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገዋል
May 30, 2026 622
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የ34ኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ጨዋታዎች ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮጵያ መድን እና መቀሌ 70 እንደርታ ከባህር ዳር ከተማ ነጥብ ተጋርተዋል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ እና ኢትዮጵያ መድን አንድ አቻ ተለያይተዋል። የወልዋሎው ጌቱ ኃይለማርያም በሰባተኛው ደቂቃ በራሱ መረብ ላይ ያስቆጠረው ግብ ኢትዮጵያ መድንን መሪ ሆኗል። የኢትዮጵያ መድኑ ጋናዊ ተጫዋች እስማኤል አብዱልጋኒዩ በ12ኛው ደቂቃ በራሱ ላይ ባስቆጠረው ግብ ወልዋሎ አቻ መሆን ችሏል። ውጤቱን ተከትሎ ወልዋሎ አዲግራት ዩኒቨርሲቲ በ41 ነጥብ 15ኛ ደረጃን ይዟል። ቡድኑ ባለፉት ሁለት ጨዋታዎች አቻ ወጥቷል። የወቅቱ የሊጉ አሸናፊ ኢትዮጵያ መድን በ43 ነጥብ ደረጃውን ከ13ኛ ወደ 12ኛ ከፍ አድርጓል። መድን ባለፉት ሶስት ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። በአበበ ቢቂላ ስታዲየም በተካሄደው ሌላኛው መርሐ ግብር መቀሌ 70 እንደርታ እና ባህር ዳር ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል። መቀሌ 70 እንደርታ በ35 ነጥብ 18ኛ ደረጃን ይዞ ወራጅ ቀጠና ውስጥ ይገኛል። ተጋጣሚው ባህር ዳር ከተማ በበኩሉ በ46 ነጥብ ከነበረበት 9ኛ ደረጃ ወደ 6ኛ ከፍ ብሏል። ‘ ባህር ዳር ከተማ በሊጉ በበርካታ ጨዋታዎች አቻ የወጣ (19 ጊዜ) ቡድን ነው። ዛሬ አስቀድመው በተደረጉ ጨዋታዎች ሲዳማ ቡና አዳማ ከተማን 1 ለ 0 በማሸነፍ መሪነቱን አጠናክሯል። በዝናብ ምክንያት ዛሬ ከቆመበት ቀጥሎ በተካሄደው ጨዋታ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ኢትዮ ኤሌክትሪክን 2 ለ 1 አሸንፏል። ጨዋታዎቹን ተከትሎ የ34ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ተጠናቋል። ፕሪሚየር ሊጉ ኢትዮጵያ ከማላዊ ጋር በምታደርጋቸው የወዳጅነት ጨዋታዎች ምክንያት የሚቋረጥ ሲሆን፣ ሰኔ 7 ቀን 2018 ዓ.ም በ35ኛ ሳምንት መርሐ ግብር ይመለሳል።
የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ወደ ዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ አለፈ
May 30, 2026 603
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 22/2018 (ኢዜአ)፦ በ2026 ከ17 ዓመት በታች ሴቶች የዓለም ዋንጫ የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ኢትዮጵያ ብሩንዲን 2 ለ 1 አሸንፋለች። በኢንትዋሪ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ዳንሲል ኢራንዚ በስምንተኛው ደቂቃ ባስቆጠረችው ጎል ብሩንዲን መሪ ሆናለች። ምኅረት አየለ በ53ኛው እና ሊዲያ እያሱ በ73ኛው ደቂቃ ከመረብ ላይ ያሳረፏቸው ግቦች ኢትዮጵያን አሸናፊ አድርገዋል። ሊዲያ እያሱ በመጀመሪያው ጨዋታ ሁለት ግቦችን ማስቆጠሯ የሚታወስ ነው። ውጤቱን ተከትሎ ኢትዮጵያ በድምር ውጤት ብሩንዲን 4 ለ 2 በማሸነፍ ወደ ዓለም ዋንጫው የመጨረሻ ዙር ማጣሪያ አልፋለች። ኢትዮጵያ በመጨረሻው ዙር ከዛምቢያ እና ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ አሸናፊ ጋር ትጫወታለች። ሁለቱ ብሔራዊ ቡድኖች በመጀመሪያ ዙር ባደረጉት ጨዋታ ዛምቢያ 5 ለ 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፋለች። የሀገራቱ የመልስ ጨዋታ ነገ ይደረጋል። ኢትዮጵያ የዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎችን በሰኔ ወር መጨረሻ እና ሐምሌ ወር መጀመሪያ ላይ ታደርጋለች። 10ኛው የፊፋ የሴቶች ከ17 ዓመት በታች ዓለም ዋንጫ በጥቅምት ወር 2019 ዓ.ም በሞሮኮ አስተናጋጅነት ይካሄዳል። በውድድሩ ላይ 24 ሀገራት ይሳተፋሉ። በዓለም ዋንጫው አፍሪካ ሞሮኮን ጨምሮ በአምስት ሀገራት ትወከላለች። ቀሪ አራት ሀገራት በማጣሪያ ጨዋታዎች ይለያሉ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም