ቀጥታ፡
መጣጥፍ
የጀጎል አለም አቀፍ ቅርስን የታደገው ሀገራዊ ለውጥ
Apr 4, 2026 197
የስልጣኔ መነሻ የጥበብ መፍለቂያ የሆነችው የምስራቋ ፈርጥ ሀረር የንግድ፣ የፖለቲካና ማህበራዊ ትስስር ማዕከል ሆና በትውልድ ቅብብሎሽ ከአንድ ሺህ አመታት በላይ የተሻገረች እድሜ ጠገብ ከተማ ነች። በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በምስራቅ አፍሪካ የእስልምና ሀይማኖት ትምህርትና የንግድ ማዕከል የነበረችው ከተማዋ በርካታ ቋሚና ተንቀሳቃሽ እንዲሁም የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቁሳዊና ሀይማኖታዊ ቅርሶችን የያዘች ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ ነች። ከእነዚህ ቅርሶች መካከል ጥንታዊ የስነ-ህንፃ የጥበብ፣ የከተማ ፕላን፣ ባህላዊ የመሬት አጠቃቀም፤ አካባቢያዊ መስተጋብርና የስልጠኔ መገለጫ በሚል እኤአ በ2006 በተባበሩት መንግስታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ተቋም ዩኔስኮ በአለም አቀፍ ቅርስነት የተመዘገበው የጀጎል ቅርስ ይጠቀሳል፡፡   ቅርሱ ምንም እንኳን በኪነ ህንፃ ጥበብ በላቁ በአርቆ አሳቢ አባቶች እንዳይፈርስና ሚዛኑን ጠብቆ ለረጅም ጊዜ እንዲቆይ በተመረጠ ድንጋይ እና አፈር በልዩ ጥበብ የተገነባ ቢሆንም በጥበቃና እንክብካቤ ጉድለት ምክንያት ከግማሽ ምዕተ አመታት በላይ እድሜን ባስቆጠረው ቅርስ ላይ አደጋ ተጋርጦበት ቆይቷል። በቅርሱ ውስጣዊ እና ውጫዊ ክፍሎች የህገ-ወጥ ግንባታዎች መበራከትና በሌሎች ምክንያቶች በደረሰበት ጉዳት የጥንት ስልጣኔ ምልክት የሆነው አለም አቀፉ የጀጎል ቅርስ ከዩኔስኮ የአለም ቅርስነት እስከመሰረዝ የደረሰ አደጋ ተደቅኖበት ነበር። ሆኖም ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በአዲስ እሳቤ፤ በተደመረ አቅምና በላቀ ቁርጠኝነት፤ ህዝብን በማሳተፍ ከመንግስት ምንም አይነት በጀት ሳይመደብለት ከ25 ኪሎ ሜትር በላይ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች ማልማት ተቻለ። አሁን ላይ እነኛ በሸራና በጨርቅ በተሰሩ ህገወጥ ግንባታዎች ተወሮ የነበረው 3ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው የጀጎል ግንብ ዙሪያ በአበቦችና ቅርሱን በሚያስውቡ ስራዎች ደምቀዋል።   በዚህም አባቶች ከዘመኑ ቀድመው ዛሬም ድረስ ግርምትን በሚያጭር ጥበብ አንፀው ያኖሩት ይህንን የሀገር ሀብት በመታደግ ትውልዱን ከታሪክ ተወቃሽነት ወደ ዳግም ታሪክ ሰሪነት እንዲሸጋገር ማድረግ ተችሏል። ስራውም የትላንትን መሰረት ሳያናጋ፤ የቀድሞ አባቶችን ጥበብና ስልጣኔ ሳይጋፋና ሳይዘነጋ ጥንታዊውን ከዘመናዊ ጋር አዋህዶ ቅርስ መገኛ ለሆኑ ሌሎች አካባቢዎችም ተምሳሌት በሚሆን ደረጃ አስደናቂ ስራ ተከናወነ። የአካባቢውን ሀብትና እውቀት በመጠቀም እውን የተደረገው ይህ ስራ በእያንዳንዱ የሀረሪ ጥንታዊ ቤቶች በሚገኙ የታሪክ አሻራዎችና የባህል መገለጫዎች እንዲደምቅም ሆኗል። ይህ ትውልድ ተሻጋሪ ስራ ቅርሱን ከአደጋ ከመታደግ ባለፈ ከገጠር እስከ ከተማ፣ ከግለሰብ እስከ ማህበራትና የዳያስፖራ አባላት ድረስ ሁሉም በያገባኛል ስሜት አሻራውን ያኖረበት ዘመን ተሻጋሪ ፕሮጀክት ነው። ይህም በቅርሱ ላይ የእኔነት ስሜት እንዲጎለብት በማድረግ የእይታ ለውጥ እንዲመጣ ያስቻለና ቀደም ሲል የነበሩ የግለኝነት አስተሳሰቦችን በመቅረፍ የወል እሳቤ እውን የሆነበት ፕሮጀክት ሆኖ ታይቷል።   ዛሬ ላይ እነኛ የቆሻሻ መጣያ የነበሩ እና በአካባቢው ለማለፍ ከባድ የነበሩ የጀጎል መንገዶች ፀድተው ውብ ሆነዋል። ይዘታቸውን ለቀው የነበሩ ቅርሶችም የአለም ቅርስነት ክብርና መስፈርትን በሚመጥን ደረጃ ታድሰዋል። ዛሬ የጀጎል ነዋሪ እንደቀድሞ አካባቢውን ለቆ ለመሄድ ሳይሆን መኖርን የሚመርጥባት የወጣውም መመለስን የሚመኝባት ምቹ አካባቢ ሆናለች። የመቻል ምልክት የትብብር ውጤትና የአብሮነት ጉልበት በተግባር የታየበት የጁገል መልሶ ልማት ጥንታውን መንደር ለነዋሪዎች ምቹ ለጎብኚዎች ተመራጭ የጉብኝት ስፍራ እንዲሆን ማድረግ ተችሏል። በለውጡ መንግስት በአዲስ መልክና ቀለም የተዋበው ጀጎል የሀረርን ቀደምት ስልጣኔ እየመሰከረ የሀገርንም ገፅታ እየገነባ ይገኛል።
የለውጡ ትሩፋት - ግብርናን የሚያሻግረው ዕይታ
Apr 3, 2026 85
የለውጡ ትሩፋት - ግብርናን የሚያሻግረው ዕይታ በአሸናፊ በድዬ በኢትዮጵያ መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም ልዩ ቀን ሆኖ በታሪክ ተመዝግቧል። ዕለቱ አዲስ ምዕራፍ የተከፈተበትና ታሪካዊ የለውጥ ጉዞ የተጀመረበት ነው። ኢትዮጵያ ከለውጡ በኋላ በፖለቲካ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች መሠረታዊ ውጤቶችን እያስመዘገበችም ትገኛለች። በተለይ በሀገር አቀፍ የኢኮኖሚ ሪፎርም መሰረት ፈጣን፣ አስተማማኝና ዘላቂነት ያለው ኢኮኖሚ ዕድገት ለማስመዝገብ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል። ለዚህም ነው ዕድገቱን ፈጣንና ተከታታይ ለማድረግ አምስት ዋና ዋና የኢኮኖሚ ምሰሶዎች ተለይተው ወደ ሥራ የተገባው። እነዚህ ዘርፎች ኢኮኖሚው በአንድ ዘርፍ ላይ ብቻ ተንጠልጥሎ እንዳይቀርና በማንኛውም ዓለም አቀፋዊ ጫና ውስጥ የማይናወጥ ጽኑ መሠረት እንዲኖረው ያደርጋል። በተለይም ግብርናው ለኢንዱስትሪው ግብዓት ሲያቀርብ፣ ቴክኖሎጂው ደግሞ የግብርናውን ምርታማነት ሲያሳልጥ፣ ማዕድንና ቱሪዝም ደግሞ ለሌሎች ዘርፎች መስፋፋት ወሳኝ የሆነውን የውጭ ምንዛሬ ሲያመነጭ የተቀናጀ የሰንሰለት አሰራር መዘርጋት ይችላል። በዚህ መሠረት፣ ከለወጡ ወዲህ የሀገሪቷን የኢኮኖሚ ገጽታ እየቀየሩ ያሉትን እነዚህን ዘርፎችና የታሪካዊ ቀኗን ትሩፋት በወፍ በረር እንመለከታለን። 1. ግብርና ፦ የስንዴ አብዮት ግብርናው አሁንም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ነው። ከለውጥ ማግስት በኋላ ከዝናብ ጥገኝነት በመውጣትና በቴክኖሎጂ በመታገዝ በዘርፉ ታሪክ ቀያሪ ስኬት እየተመዘገበ ይገኛል። የዚህ ስኬት ዋነኛ ማሳያ ደግሞ በዓለም አቀፍ ደረጃ አድናቆትን ያተረፈው የኢትዮጵያ የስንዴ አብዮት ነው። 👉የቀድሞ ቅኝት፦ የዳራ እውነታዎችና የጥገኝነት ቀንበር ከሀገራዊ ለውጡ በፊት የኢትዮጵያ ግብርና ገጽታ በእድገት ማነቆዎች የተጠፈረ ነበር። ኢትዮጵያ ሰፊ ለም መሬት፣ አመቺ የአየር ንብረትና ብዙ የሰው ኃይል እያላት ለዓመታዊ የፍጆታ ፍላጎቷ የሚሆን በቂ ስንዴ ማምረት አቅቷት ለዓመታት ቆይታለች። በዚህም ምክንያት በየዓመቱ ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ በሚደርስ የውጭ ምንዛሬ ስንዴ በመግዛት ከውጭ ለማስገባት ትገደድ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ታሪኳ ነው። የዚህ ዓይነቱ አካሄድ ኢትዮጵያ የማምረት አቅም እያላት ለውጪ ምንዛሪ ወጪ ዳርጓት ቆይቷል፤ በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ የሚፈጠሩ የዋጋ መዋዠቆችና ጂኦ-ፖለቲካዊ ቀውሶች ተጋለጭነቷን አስፍቶት እንደነበር የሚታይ እውነት ነው። 👉የለውጡ ስትራቴጂና ቁርጠኝነት የስኬት ጅማሮ ይህ ቢያንስ በስንዴ ጥገኛ አድርጎን የቆየው ተግዳሮት ታሪክ በሚቀይር መልኩ አዲስ ምዕራፍ ያስከፈተው መጋቢት 24 ቀን 2018 ዓ.ም የተጀመረው ሀገራዊ ለውጥ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነትና ያላሰለሰ ክትትል የተጀመረው የተቀናጀ ጥረት የኢትዮጵያን ግብርና ከነበረበት ተግዳሮት አላቆ ዘመናዊና ውጤታማ ምዕራፍ ያሸጋገረው ጉዞ ጀምሯል። ለዚህ በአብነት የሚጠቀሰው የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ስትራቴጂ ነው። በ2011 ዓ.ም በሙከራ ደረጃ በ3 ሺህ 500 ሄክታር መሬት ላይ ብቻ የተጀመረው የመስኖ ስንዴ ልማት፣ ዘንድሮ አራት ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ሄክታር ደርሷል፡፡ የምርት መጠኑም ከ100 ሺህ ኩንታል ወደ 175 ሚሊዮን ኩንታል ከፍ ብሏል፡፡ በአሁኑ ወቅት በመኸር፣ በበልግና በመስኖ የሚለማው መሬት ስፋት ከሀገራዊ ለውጡ በፊት ካለው ጋር ሲነጻጸር እምርታዊ ለውጥ ማሳየቱን ማስተዋል ይቻላል። በዚህም ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀዳሚ ስንዴ አምራች ሆናለች። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ባሳለፍነው ዓመት ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በኢኮኖሚው ዘርፍ ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ኢትዮጵያ በአፍሪካ አንደኛ ስንዴ አምራች ሀገር መሆኗን መግለጻቸውን ይታወሳል። ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ የጀመረችው ስትራቴጂያዊ ንቅናቄ በሀገሪቷ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ የምርት ዕድገት አስመዝግቧል። ይህም የዘርፉን ጉዞ ከነበረበት ዝቅተኛ ደረጃ አላቆ በአጭር ጊዜ ውስጥ በብዙ እጥፍ እንዲልቅና ለሀገራዊ የምግብ ሉዓላዊነት ዋነኛ መሰረት እንዲሆን አስችሎታል። 👉የምግብ ሉዓላዊነትና የሀገር ክብር ዛሬ ኢትዮጵያ ስንዴን ከውጭ ከማስገባት መላቀቅ ብቻ ሳይሆን፣ ስንዴ ለውጭ ገበያ መላክ የጀመረችበት አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ላይ ትገኛለች። ይህም የለወጡ ትሩፋት ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬን በማዳን፣ በዓለም አቀፍ መድረክ የኢትዮጵያን ተደራዳሪነትና ክብር ከፍ አድርጓል። በተጨማሪም እንደ አረንጓዴ አሻራ፣ የሌማት ትሩፋትና መሰል መርሃ-ግብሮች በዘርፉ እምርታዊ ለውጥ እያመጡ ይገኛሉ። 2. ኢንዱስትሪ የኢንዱስትሪው ዘርፍ በተለይም አምራች ኢንዱስትሪው ከመጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም ወዲህ የሀገር ውስጥ ምርትን በመተካትና ለውጭ ገበያ የሚሆን ጥራት ያለው ምርት በማቅረብ ላይ ያተኮረ ነው። በ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ አማካኝነት ከዚህ ቀደም ተዘግተው የነበሩ በርካታ ፋብሪካዎች ወደ ሥራ ተመልሰዋል። የኮንስትራክሽን ግብዓቶችን (እንደ ሲሚንቶና ብረት) በሀገር ውስጥ የማምረት አቅም በማደጉ የግንባታ ዘርፉን አነቃቅቷል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመነትን በመሳብ ለሺዎች የሥራ ዕድል ፈጥረዋል። 3. ማዕድን ኢትዮጵያ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት በሳይንሳዊ መንገድ በመጠቀም የውጭ ምንዛሬ ግኝቷን ለማሳደግ ከለውጡ ወዲህ ትልቅ ርብርብ እየተደረገ ነው። የወርቅ፣ የድንጋይ ከሰልና የሌሎች ማዕድናት ምርት በከፍተኛ ሁኔታ አድጓል። በተለይ የድንጋይ ከሰልን በሀገር ውስጥ ማምረት መቻሉ ለሲሚንቶ ፋብሪካዎች የሚወጣውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ቀንሷል። በዘርፉ ሕገ-ወጥ ዝውውርን በመቆጣጠርና ዘመናዊ አሰራርን በመዘርጋት የመንግሥት ገቢ እንዲያድግ ተደርጓል። 4. ቱሪዝም ከመጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም ወዲህ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመጪነትና ተግባራዊ ስራዎች ቱሪዝም በአዲስ መልክ የተወለደና ትልቅ ተስፋ የተጣለበት ዘርፍ ሆኗል። ቀደም ሲል በታሪካዊና ተፈጥሯዊ ቅርሶች ላይ ብቻ ተወስኖ የቆየው እንቅስቃሴ፣ አሁን ላይ ሰው ሰራሽ መስህቦችን በማካተት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቱን አረጋግጧል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተገነቡት አንድነት፣ እንጦጦና ወዳጅነት ፓርኮች የአዲስ አበባን ገጽታ ሙሉ በሙሉ ከመቀየራቸውም በላይ ለከተማ ቱሪዝም አዲስ ምዕራፍ ከፍተዋል። በ"ገበታ ለሀገር" መርሃ-ግብር የተገነቡትና በቅርቡ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት የሆኑት እንደ ወንጪ (Eco-Tourism)፣ ጎርጎራ ያሉ መዳረሻዎች የሀገሪቷን የቱሪዝም ሀብት ወደ ክልሎች በማስፋፋት ረገድ ትልቅ ስኬት አስመዝግበዋል። በቅርቡ ተመርቆ ወደ ሥራ የገባው የታላቁ ቤተ-መንግሥት የቱሪስት መዳረሻ እና በ"ገበታ ለትውልድ" ስር እየተገነቡ ያሉ ፕሮጀክቶች ዘርፉን ይበልጥ አጠናክረውታል። አዲስ አበባ የአፍሪካ መዲና በመሆኗ፣ በትላልቅ ስብሰባዎች አማካኝነት የሚገኘው ገቢ በከፍተኛ ሁኔታ አድጓል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባዔ ላይ የከተማ አስተዳደሩን የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ያስታወቁት፤ አዲስ አበባን የቱሪዝም ኮንፍረንስ ማዕከል ለማድረግ የተከናወኑ በርካታ የልማት ሥራዎችና ሜጋ ፕሮጀክቶች ፍሬ ማፍራት በመጀመራቸው፣ በከተማዋ የሚካሄዱ ኩነቶች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን ነው። በዚህም ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ ብቻ 150 የሚሆኑ አህጉር አቀፍና ዓለም አቀፍ ኹነቶች በአዲስ አበባ የተካሄዱ ሲሆን፤ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ50 በመቶ ዕድገት ማሳየቱን መግለጻቸው ይታወቃል። ከሀገር ውስጥና ከውጭ ሀገር የቱሪስት ፍሰት ጋር ተያይዞ ባለፉት ስድስት ወራት 155 ቢሊየን ብር ወደ ኢኮኖሚው ፈሰስ መደረጉን የገለጹ ሲሆን፤ መዲናዋን የቱሪዝም ኮንፍረንስ ማዕከል ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ለኹነቶቹ መጨመር በተጨባጭ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ናቸው ብለዋል። የአዲስ አበባ ከተማን ጨምሮ በክልሎች ከተሞች እየተሰሩ ያሉት የኮሪደር ልማቶች ከተማዎቹን ልዩና ውብ ከማድረጋቸው ባሻገር ለቱሪስት መስህብ ሆነዋል። 5. ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ/ዲጂታል ኢኮኖሚ ይህ ዘርፍ የኢኮኖሚ ምሰሶዎችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመደገፍ ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ የሚያደርግ ከመጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም ለውጥ ወዲህ የደመቀ የለውጥ ሞተር ነው። የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025" ስኬቶች በርካታ የመንግሥት አገልግሎቶች (ፓስፖርት፣ ንግድ ፈቃድና ታክስ ክፍያ) በበይነ-መረብ በመሆናቸው ሌብነትንና እንግልትን ይቀንሳሉ። በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች በ"ፋይዳ" መታወቂያ የታቀፉ ሲሆን፤ በ"ቴሌ ብር"ና መሰል አማራጮች የገንዘብ ዝውውር መዘመን ችሏል። የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ወደ ሥራ መግባት የአገልግሎት ጥራትንና ተደራሽነትን ጨምሯል። የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ራዕይ የ2025 ስኬትን መሠረት በማድረግ አሁን ላይ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን (AI) በስፋት የመጠቀም ግብ ወዳለው ቀጣይ ምዕራፍ ተሸጋግሯል። በ"ኢትዮ-ኮደሮች" መርሃ-ግብር አምስት ሚሊዮን ወጣቶችን በዲጂታል ክህሎት ለማሰልጠን እየተሠራ ያለው ሥራ ወጣቶችን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እያደረገም ይገኛል። እነዚህ አምስት ምሰሶዎች ተነጣጥለው የሚታዩ ሳይሆን አንዱ ሌላውን የሚደግፉ ናቸው። ይህ ታሪካዊ ለውጥ ኢትዮጵያን ወደ ብልጽግና ማማ የሚያሸጋግር ስትራቴጂ ነው። የነገዋ ኢትዮጵያ በራሷ የምትመገብና ለሌሎችም የምትተርፍ ጠንካራ ሀገር መሆኗን ያረጋገጠ ታርካዊ ክንውን ነው።
ከመጋቢት ሥጦታዎች መካከል - የጉባ ብሥራቶች  
Apr 2, 2026 2142
በዮሐንስ ደርበው የብርቱዎቹ ልጆች ብርታት በቀጣይ ...! ተከፍሎ የማያልቅ የኢትዮጵያ እና ሕዝቧ ውለታ አለብን - የመናዊያን ፍልሰተኞች ሥልጣኔ - በምርጫ ካርድ መሪን መምረጥ! መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም በኢትዮጵያ የለውጥ ብሥራት ከጫፍ እስከ ጫፍ የተሰማበት ነው። በለውጡ የስምንት ዓመታት ፈጣን ጉዞ በየዘርፉ ይበል የሚያሰኙ አመርቂ ሥራዎች ተከናውነዋል፤ ስኬቶች ተመዝግበዋል። በስምንት ዓመት ጉዞ ውስጥ ከስኬት ወደ ስኬት በመሻገር በርካታ ተግባራት ተሠርተዋል። የሀገሪቷን ቀጣይና ዘላቂ እድገት የሚያተልሙ፣ ሕዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ውጤታማ ተግባራት የተከናወነባቸው ስምንት ዓመታት አልፈዋል። ሌሎች ሜጋ ፕሮጀክቶችን ለማስጀመር ቃል በመግባት የተግባር እርምጃ ተጀምሯል። • የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ መመረቅን ተከትሎ ይፋ የተደረጉ ሜጋ ፕሮጀክቶች - የጉባ ብሥራቶች ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተመርቋል። በዚሁ ወቅት ለመላው ኢትዮጵያውያንና ለኢትዮጵያ ወዳጆች እንኳን ደስ አላችሁ፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለጥቁር ሕዝቦች ሁሉ ታሪክ ሆኖ የሚቀጥል ገድል ነው ብለዋል። የግድቡ ግንባታ ተጠናቆ ኢትዮጵያ ወደ ሌላ ምዕራፍ እንደምትሸጋገር አብሥረዋል። በቀጣይ የሚገነቡ ሜጋ ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶችንም ጉባ ላይ ይፋ አድርገዋል። ለፕሮጀክቶቹ ከ30 ቢሊየን ዶላር በላይ ወጪ ይደረጋል። እነዚህ ፕሮጀክቶችም፤ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ፣ የጋዝ ፋብሪካ ማስመረቅ፣ የነዳጅ ማጣሪያ ግንባታ፣ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ ሁለተኛው የጋዝ ፋብሪካ ግንባታ፣ የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ እና ከ1 ነጥብ 5 ሚሊየን በላይ ቤቶችን መገንባት የሚሉት ናቸው። እነዚህ የለውጡ መንግሥት ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ስትራቴጂያዊ ፕሮጀክቶችን ነድፋ እየሠራች መሆኗን ያረጋግጣሉ። ለዚህም ማሳያ የጉባ ብሥራቶች በታቀደላቸው የጊዜ ገደብ ሲጠናቀቁ ኢትዮጵያ በቀጣናው ያላትን የኢኮኖሚ ዐቅም ያጠናክራሉ። • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያኔ ካበሠሯቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች መካከል አብዛኞቹ ወደ ትግበራ ምዕራፍ ተሸጋግረዋል። ወር ባልሞላ ጊዜም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) መስከረም 22 ቀን 2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ከዳንጎቴ ግሩፕ ጋር በመተባበር የሚገነባውን የዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካ የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል። በዚሁ ወቅትም የማዳበሪያ ፋብሪካው በዓመት 3 ሚሊየን ቶን ማዳበሪያ አምርቶ ያቀርባል ማለታቸው ይታወሳል። ሕዳር 29 ቀን 2018 ዓ.ም ደግሞ የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ልማት መርሐ-ግብር ማስጀመሪያና የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ኮሚሽን ሥራ ማስጀመሪያ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኢነርጂ ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ በወቅቱ፤ የኢትዮጵያ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ልማት የኃይል ደኅንነትን በማረጋገጥ ኢኮኖሚያዊ ሽግግርና የረጅም ጊዜ የመቋቋም ዐቅም ግንባታ ላይ የተመሠረተ ብሔራዊ የልማት ተነሳሽነት ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ንጹህ የኃይል አቅርቦት የማመንጨት ዐቅምን በማላቅ በጤና፣ ግብርና፣ በኢንዱስትሪ እና የምርምር ትግበራ ማዕቀፍ የተቃኘ መሆኑንም ነው ያብራሩት። በተመሳሳይ መስከረም 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) በሶማሌ ክልል ካሉብ በዓመት 111 ሚሊየን ሊትር ማምረት የሚችለውን የኦጋዴን ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ ፕሮጀክት የመጀመሪያ ዙር መርቀዋል። ከዚሁ ጎን ለጎን የጎዴ ነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካ ግንባታ የመሠረት ድንጋይም አስቀምጠዋል። የጎዴ ነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካ ግንባታ ሲጠናቀቅ፤ የኢትዮጵያን የናፍጣ እና የቤንዚን ፍላጎት ከ80 እስከ 90 በመቶ የመሸፈን ዐቅም እንዳለው በዚሁ ወቅት የማዕድን ሚኒስትር ሀብታሙ ተገኝ (ኢ/ር) መናገራቸው ይታወሳል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ሥራን ጥር 2 ቀን 2018 ዓ.ም የመሠረት ድንጋይ በማስቀመጥ አስጀምረዋል። በወቅቱም፤ አውሮፕላን ማረፊያው በአፍሪካ ታሪክ ትልቁ የአየር ትራንስፖርት መሠረተ-ልማት ፕሮጀክት እንደሚሆን ተመልክቷል። ይህም ከኢትዮጵያ ሀገራዊ የኢኮኖሚ ሪፎርም፣ የኢንዱስትሪ ማስፋፊያ አጀንዳ እና የረጅም ዘመን የአቪዬሽን ስትራቴጂ ጋር የተናበበ መሆኑን አስገንዝበዋል። ግንባታው ሲጠናቀቅም አፍሪካን ከዓለም ቀዳሚ የአየር ትራንስፖርት መናኸሪያዎች አንዷ የሚያደርጋትን በዓመት 110 ሚሊየን መንገደኞችን የማስተናገድ ዐቅም ይኖረዋል። ከወትሮው በተለየ በጾም ወቅት እንዲዘወተሩ የሚመከሩ ምግቦች አሉ? ባሳለፍነው ሳምንት ...   • በአጠቃላይ የጉባ ብሥራቶች የኢትዮጵያን ዕድገት በማሳለጥ ሂደት የጎላ ድርሻ አላቸው። ፕሮጀክቶቹ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቁ፣ በሥራ ዕድል ፈጠራ ብሎም በኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ ሚና ያበረክታሉ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት እንድትሆንም ያስችላሉ። እነዚህ ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያ በኃይል አቅርቦት ያላትን ዐቅም በማሳደግ፤ ኢንቨስትመንት በመሳብ እና የውጭ ምንዛሪን በማሳደግ፣ መሠረተ-ልማቶችን በማስፋፋት ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንደሚኖራቸው ይታመናል። ከለውጡ ወዲህ ኢትዮጵያ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ጀምራ የመጨረስ ዐቅሟ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መሆኑን እያየን ነው። በቀጣይም የጀመረቻቸውን ሜጋ ፕሮጀክቶች ባሰበችው ጊዜ እንደምታጠናቅቅ እሙን ነው።
የሀገራዊ ለውጡ አዲስ ምዕራፍ - የሌማት ትሩፋት
Apr 1, 2026 350
ሀገራዊ ለውጡ ከመጣ ከመጋቢት 24/2010 በኋላ ትኩረት ከተሰጣቸውና ተተግብረው ስኬታማ ከሆኑት የልማት ኢኒሼቲቮች መካከል አንዱ የሌማት ትሩፋት ነው። የሌማት ትሩፋት በዋናነት የከተማና የገጠር አርሶ አደሮችን በማቀናጀት፣ በአነስተኛ ቦታ ላይ ሁሉ የጓሮ አትክልትና የዶሮ እርባታን በማስፋፋት በርካታ ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረገ ፕሮግራም ነው። የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚያግዙ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን ማለትም ወተት፣ ሥጋ፣ አሳ፣ እንቁላልና ማርን እንዲሁም አትክልትና ፍራፍሬን በስፋት በማምረት የሥርዓተ-ምግብ ማሻሻልን ዓላማ በማድረግ እየተተገበረ ያለ ሀገራዊ ኢኒሼቲቭ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሌማት ትሩፋትን በጥቅምት ወር 2015 ዓ.ም በአርባምንጭ ከተማ በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት በምግብ ራስን አለመቻል የሀገርን ክብር ይነካል፣ ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ካልቻለች ሙሉ ነፃነት ሊኖራት አይችልም ማለታቸው ይታወሳል። በስንዴ ምርት የታየው ስኬት ወደ እንስሳት ሀብት ልማት (ወተት፣ እንቁላል፣ ስጋና ማር) መደገም እንዳለበትም አሳስበው ጤናማና አምራች ትውልድ ለመፍጠር ሌማታችንን በተመጣጠነ ምግብ መሙላት አለብን በማለት ማስገንዘባቸውም እንዲሁ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በቂ እና አመርቂ ምግብ ማግኘት መሆኑን በመጠቆም በቂ የመጠን፣ አመርቂ ደግሞ የይዘት ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። የሌማት ትሩፋት ግብ በቤተሰብ ደረጃ የተመጣጠነ ምግብን ተደራሽ በማድረግ የህፃናት መቀንጨርን መቀነስ፣ ለወጣቶችና ለሴቶች ሰፊ የሥራ ዕድል መፍጠር፣ እንዲሁም ከሀገር ውስጥ ፍጆታ የተረፈውን ምርት ለውጭ ገበያ በማቅረብ የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ግኝት ማሳደግና የዜጎችን የኑሮ ደረጃ በዘላቂነት ማሻሻል መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ይህ ሀገራዊ ኢኒሼቲቭ የተለያዩ የትኩረት መስኮች አሉት። የላሞችን ዝርያ ማሻሻልና የወተት ምርትን ማሳደግ፣ የእንቁላልና የዶሮ ሥጋ ምርትን በየቤተሰቡ ተደራሽ ማድረግ፣ ዘመናዊ ቀፎዎችን በመጠቀም የማር ምርትን በጥራትና በብዛት መጨመር እንዲሁም ጥራት ያለው የስጋ ምርት ማቅረብ ቁልፍ ምሰሶዎች ናቸው። ግብርናና የእንስሳት እርባታን የከተማ ግብርና አካል የማድረግ ሰፊ ንቅናቄ መፈጠሩ ከታዩ ለውጦች መካከል የሚጠቀስ ነው። የዶሮና የእንቁላል ምርት በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል። በብዙ ክልሎች የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎችና የምርት መሰብሰቢያ እና ማከማቻ ማዕከላት ተስፋፍተዋል። የሌማት ትሩፋት ለወጣቶችና ለሴቶች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር የገቢ ምንጭ ሆኗል። ከመደበኛው የሰብል ምርት በተጓዳኝ አርሶ አደሩ በየቀኑ ገቢ ማግኘት መቻሉ የኑሮ ደረጃው እንዲሻሻል በእጅጉ አግዟል። በፕሮቲን የበለፀጉ ምግቦችን ለህጻናትና ለነፍሰ ጡር እናቶች ተደራሽ በማድረግ በኩል ለውጥ መታየቱን የግብርና ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። በሀገር አቀፍ ደረጃ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የአንድ ቀን ጫጩቶች፣ የተሻሻሉ የወተት ላሞችና ዘመናዊ የንብ ቀፎዎች ለአርሶ አደሩና ለከተማ ነዋሪው ተደራሽ መደረጋቸው፣ ቀደም ሲል በግዢ ብቻ ይሟሉ የነበሩ የእንቁላል፣ የወተትና የማር ምርቶች አሁን ላይ በብዙ ቤተሰቦች ጓሮ እንዲመረቱ አድርጓል። ይህ ተሞክሮ በቤተሰብ ደረጃ የፕሮቲን አቅርቦትን በማሳደግ በሕፃናት ላይ የሚታየውን የምግብ እጥረትና መቀጨጭ ለመቀነስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ሲሆን በተለይም የከተማ ግብርናን በማስፋት ነዋሪው በውስን ቦታ ምርታማ መሆን እንደሚችል በተግባር የታየበት እንደመሆኑ በምግብ ራስን የመቻል ጉዞ ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ታይተዋል። በተጨማሪም፣ ጥራት ያለው የማርና የሥጋ ምርት ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የተጀመሩ ጥረቶች የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ግኝት ለማሳደግ አዲስ በር ከፍተዋል። የሌማት ትሩፋት ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ለመቻልና የዜጎቿን የአመጋገብ ሥርዓት ለማሻሻል የጀመረችው ስትራቴጂካዊ ጉዞ አካል ሲሆን፣ ከመነሻው አንስቶ በምርት ዕድገት፣ በሥራ ዕድል ፈጠራና በሥራ ባህል ለውጥ ረገድ ተስፋ ሰጪ ውጤቶችን አሳይቷል። ይህ ንቅናቄ በተለይ የእንስሳት ተዋጽኦን በየጓሮውና በየቤቱ ተደራሽ በማድረግ በሕፃናት ላይ የሚታየውን የመቀንጨር እና የመቀጨጭ ችግር ለመቅረፍና አነስተኛ አምራቾችን የዕለት ገቢ ባለቤት ማድረግ አስችሏል። የሌማት ትሩፋት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የሥነ ምግብ ሚዛን መዛባትን ለማስተካከል አርሶ እና አርብቶ አደሩም ይሁን የከተማ ነዋሪው በአካባቢው ያሉ አቅሞችን ሁሉ ወደ ልማት በመቀየር ሌማቱን ከመሙላት ባሻገር ለሌሎች ለመትረፍ የሚተጉበት ሀገራዊ ለውጡ ያስገኘወ ስኬታማ የንቅናቄ ፕሮግራም ነው፡፡ በአጠቃላይ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለዘላቂ ብልጽግና መሠረት የሚጥል ታላቅ ብሔራዊ ፕሮግራመ መሆኑን በተጨባጭ እያረጋገጠ ነው።
በኢዜአ ዐይን …!  
Mar 29, 2026 3050
በዮሐንስ ደርበው ሥልጣኔ - በምርጫ ካርድ መምረጥ በያዝነው ዓመት ወርኃ ግንቦት በባተ 24ኛው ቀን ኢትዮጵያ 7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ ለማካሄድ ቀን ቆርጣለች። ለዚህም ቅድመ ዝግጅቶችን በማጠናቀቅና የጊዜ ሰሌዳ በማውጣት ወደ ትግበራ ምዕራፍ ገብታለች። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምርጫውን ተዓማኒ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውን፤ ቀሪ ሥራዎችም እየተከናወኑ መሆኑን ገልጿል። ለዚህም የምርጫ ሕጉን ከማሻሻል ጀምሮ በቴክኖሎጂ የታገዙ ሥርዓቶች ወደ ሥራ መግባታቸው በአሥረጂነት ይጠቀሳሉ። በተጨማሪም የምርጫ ትምህርትና ግንዛቤን ለማስፋት ለሚሠሩ በርካታ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ፈቃድ መሰጠቱ፤የምርጫ ሂደትን ፍትሐዊነት ለማረጋገጥም በርካታ የሀገር ውስጥ ድርጅቶች በኦንላይን ሥርዓት በታዛቢነት መመዝገባቸውን አስረድቷል። በኢዜአ ዐይን …! በገበታ ለሀገር የተገለጠው የተደመረ ዐቅም - ለኢትዮጵያ ስኬቶች እንደማሳያ የጤና ነገር … እንዲሁም ዐለም ዐቀፍ ታዛቢዎች በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አማካኝነት መጥተው ፈቃድ የሚወስዱበት ዝግጅት እየተደረገ ነው። ምርጫ ቦርድ ለመራጮች ምዝገባ አወዳድሮና ገለልተኝነታቸውን በፖለቲካ ፓርቲዎች አስተችቶ ያሠለጠናቸውን 187 ሺህ 28 የምርጫ አስፈጻሚዎች አሠማርቷል። ለመራጮች ምዝገባ የተዘጋጁ 46 ሺህ 757 ጣቢያዎች እና ተጨማሪ በርካታ ንዑስ ጣቢያዎችም ተሠናድተዋል። እንደ ምርጫ ቦርድ መረጃ፤ 46 የፖለቲካ ፓርቲዎች በዘንድሮው ምርጫ ለውድድር ተመዝግበዋል። በሌላ በኩል ደግሞ 73 ዕጩዎች በግል ለውድድር መቅረባቸው ተገልጿል። ምርጫ ነፃ፣ ሰላማዊና ፍትሐዊ ሆኖ የሚከናወነው ሁሉም ፓርቲ ሕግን አክብሮ ኃላፊነቱን ሲወጣ እንደሆነ ያስማማል። የምርጫው ስኬት የሚረጋገጠውም ቦርዱ ለብቻው በሚያደርገው ጥረት ሳይሆን፤ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ዕኩል ኃላፊነቱን መወጣት ሲችል መሆኑ ይታመናል። በመሆኑም በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚወዳደሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሰባት ምዕራፎችና በ30 አንቀጾች የቀረበውን የምርጫ ሥነ-ምግባር ደንብ ፈርመዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በምርጫ ሂደት የዜጎችን ተሳትፎ ለማበረታታት “ምርጫችን ነው-ሀገር ያለኛ” የተሰኘ የምርጫ ኅብረ-ዝማሬ ማስመረቁ ይታወቃል። በዚሁ ወቅት የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ፤ ኅብረ-ዝማሬው አካታች ተሣትፎን ለማበረታታት መሠናዳቱን አስገንዝበዋል። የልዩ ልዩ ድምጾች ኅብራዊነት ያለውን የጋራ ጥንካሬ በማሳየት በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የዜጎችን ተሳትፎ ማጎልበት የኅብረ-ዝማሬው ዓላማ መሆኑም ተገልጿል። በ6ኛው ጠቅላላ ምርጫም “የሀገር ካስማ” የተሰኘ ኅብረ-ዝማሬ ይፋ መደረጉ ይታወሳል። ከየካቲት 28 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በግንቦት ወር ለሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የመራጮች ምዝገባ እየተከናወነ ነው። እስካሁን ባለው መረጃ ምዝገባው እስከ መጋቢት 28 ቀን 2018 ዓ.ም ይቀጥላል። የመራጮች ምዝገባ እየተከናወነ የሚገኘውም፤ በመደበኛ የመራጮች ምዝገባ (ማኑዋል)፣ ምርጫዬ በተሰኘ የሞባይል መተግበሪያ እና በድረ ገጽ ነው። ከአጠቃላይ የምርጫ ጣቢያዎች መካከል በ17 ሺህ ያህሉ የዲጂታል የመራጮች ምዝገባን ተደራሽ ለማድረግ ሲሠራ መቆየቱን ቦርዱ ማሳወቁ ይታወሳል። በዚህም መሠረት ከየካቲት 28 ቀን 2018 ዓ.ም. እስከ መጋቢት 18 ቀን 2018 ዓ.ም. በማንዋልና በዲጂታል አማራጭ በተከናወነ የመራጮች ምዝገባ ከ28 ሚሊየን 365 ሺህ 310 በላይ መራጮች ተመዝግበዋል። በኢትዮጵያ የምርጫ፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ እና የምርጫ ሥነ-ምግባር ዐዋጅ ቁጥር 1162/2011 አንቀጽ 37(7) ላይ ቦርዱ በድምፅ መስጫ ወረቀት ላይ የዕጩዎች ምሥልና የመለያ ምልክቶችን አቀማመጥ፣ ቅደም ተከተልና እንዲሁም ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮች ለተወዳዳሪ ፓርቲዎች እና የግል ዕጩዎች ግልጽ በሆነ መንገድ በመመሪያ እንደሚወስን ይደነግጋል። በዚህም መሠረት ምርጫ ቦርድ የፖለቲካ ፓርቲ ዕጩዎች በድምፅ መስጫ ወረቀት ላይ የሚኖራቸውን ቅደም ተከተል ለመወሠን የሚያስችለውን የዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓት ባሳለፍነው መጋቢት 14 ቀን በይፋ አስጀምሯል። የድምፅ መስጫ ወረቀት ኅትመት የሚከናወነው በድምፅ መስጫ ወረቀት ላይ የዕጩዎች ምሥልና የመለያ ምልክት አቀማመጥን የሚወሥነው የዕጣ ማውጣት ሂደት መጠናቀቅን ተከትሎ መሆኑ ይታወቃል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መጋቢት 19 ቀን 2018 ዓ.ም. የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የፖለቲካ ፓርቲዎች ነፃ የዓየር ሠዓት ድልድል የዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓት አካሂዷል። በዚህም መሠረት በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለሚወዳደሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በ24 ሬዲዮ፣ በ20 ቴሌቪዥን እና በ6 ጋዜጦች በሕዝብና በንግድ ሚዲያዎች ነጻ የዓየር ሠዓት ተድልድሎላቸዋል። የሠዓት ድልድሉ ፖለቲካ ፓርቲዎች ፕሮግራማቸውንና ፖሊሲዎቻቸውን እንዲያስተዋውቁ፣ የግል ዕጩዎችም አማራጭ ሐሳባቻቸውን እንዲያጋሩና የምርጫ ቅስቀሳ እንዲያደርጉ ብሎም ከመራጩ ጋር እንዲተዋወቁ ዕድል የሚሰጥ ነው። ይፋ በተደረገው ነፃ የዓየር ሠዓት የተመዘገቡ 46 የፖለቲካ ፓርቲዎችና የግል ዕጩዎች በኃላፊነት ስሜት እንዲጠቀሙ ይጠበቃል። በአጠቃላይ በምርጫ ካርድ መሪን መምረጥ ከሥልጣኔ ቁንጮዎች አንዱ ሆኖ ይነሳል። የመራጮች ምዝገባ ሂደትም የሕዝቡን ዴሞክራሲያዊ ልምምድ ያጎለብታል። ምርጫ፤ ዜጎች ሕገ-መንግሥታዊ መብታቸውን እንዲጠቀሙ፣ ተቋማዊ አሠራርን እንዲያጠናክሩ ብሎም በካርዳቸው ይሁንታ የሚመራቸውን መምረጫ ቁልፍ ነው። ኢትዮጵያ በወሳኝ የምርጫ ወቅት ላይ ናትና፤ ለስኬታማነቱ ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል። #ምርጫ #ኢዜአ #የኢትዮጵያ_ዜና_አገልግሎት #Ethiopian_News_Agency #የመራጮች_ምዝገባ #በኢዜአ_ዐይን
ተከፍሎ የማያልቅ የኢትዮጵያ እና ሕዝቧ ውለታ አለብን - የመናዊያን ፍልሰተኞች
Mar 19, 2026 2475
በዮሐንስ ደርበው ምድረ ቀደምቷ ሀገር ኢትዮጵያ ለተገፉ፣ ጥላ ከለላ ለሚሹ፣ ለተከዙና ለታረዙ የሀገራት ዜጎች መጠጊያ ናት። የኢትዮጵያን ቸርነትም ከተጠለሉባት እንግዶቿ በላይ ምሥክር የለም። የኢትዮጵያን ደጅ የረገጡ ሁሉ በቆይታቸው ለተደረገላቸው ሁሉ ‘ውለታችንን በምን እንክፈል’ ሲሉ ይደመጣሉ። ከአያሌ ሀገራት በመልከ ብዙ ቀውሶች ሳቢያ ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ሁሉ የቆሰሉ ልባቸው ታክሞ፣ ዕንባቸው ታብሶና ሕይወታቸው ታድሶ ኑራቸውን አደላድለዋል። የብርቱዎቹ ልጆች ብርታት በቀጣይ ...! በዚህም ከአፍሪካም ሆነ ከተቀረው ክፍላተ ዓለም የጦርነትና ግጭት ጥላ ያጠላባቸውና ሰላምን የተጠሙ የቀጣናው ሀገራት ዜጎች ኢትዮጵያን ሲሹ ማየት የተለመደ ነው። የየመን ዜጎች ለዚህ ማሳያ ናቸው። ኢብቲሳም ኻሊድ እና መሰል የመናዊያን ከየመን የእርስ በርስ ግጭት በኋላ የኢትዮጵያን ደጅ ረግጠው ዛሬ ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች የሚተርፍ የተድላ ኑሮ እየኖሩ ነው። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረገችው ኢብቲሳም እንደምትለው፤ በየመን አለመረጋጋት በፈጠረው ጠባሳ እርሷና መሰሎቿ ለፍልሰት ተዳርገዋል። ለዚህ ደግሞ ምርጫቸው ኢትዮጵያ ሆነች። ወደ ኢትዮጵያም መጥተው የሀገሬው ፊት ሳይኮሰኩሳቸው በፍቅር እንደተቀበሏቸው ትናገራለች። በዚህም ዛሬ የመናዊያን ተስፋቸው ለምልሞ፣ ሕይወታቸው ሠምሮ ኢትዮጵያን እንደ እናት ቆጥረው እየኖሩ ስለመሆኑ ትናገራለች። ከ11 ዓመታት በፊት ወደ ኢትዮጵያ የመጣችው ኢብቲሳም፤ በወቅቱ ቀኑ እንደጨለመባት ታወሳለች። ሰው ከቤቱ፣ ከወገኑ…ከሀገሩ ወጥቶ ወዴት ይሄዳል? በወቅቱ የነበረውን ጭንቀት ማየልም ታስታውሳለች። አሁን ግን ስለ ኢትዮጵያ እና ሕዝቧ በጎነት ዐውርታ አትጠግብም። “አሁን ፍልሰተኛ አይደለሁም፤ ያለሁት በሁለተኛዋ ሀገሬ ኢትዮጵያ ነውና” ትላለች። እንዲህ ባለው የረመዳን ወቅት ደግሞ የፍልሰተኞች ሁሉ ሰብሳቢ ናት። “ሁሉም ከእነ ቤተሰቡ ወደ ቤቷ እየመጣ ያፈጥራል። በዚህም በፍልሰት እንደመጡ ሳይሆን ቤተሰባዊነት ይሰማቸዋል። ከየመን፣ ሱዳን፣ ሶማሊያ፣ ኤርትራ፣ አፍጋኒስታን፣ ኮንጎሊዝ (DRC) ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ሁሉ ሰብሰብ ብለው የኢፍጣር መርሐ-ግብርን እንደሚያከናውኑም ታነሳለች። በዚህ ላይ ኢትዮጵያውያን ብርታት ናቸው ትላለች፤ ሁሌም ‘አይዟችሁ፣ በርቱ፣ ነገ ጥሩ ይሆናል’ እያሉ ያበረቱናል፤ ክብርና ፍቅር ይሰጡናል ስትልም ታስረዳለች። የኢትዮጵያንና ሕዝቧን ውለታ እንዴት መክፈል ይቻላል? ኢትዮጵያን ሀገራችን ብለን ነው እየጠራን ያለነው። እንደ እንግዳ እንደ ፍልሰተኛ እራሳችንን አናስብም፤ እንደሀገሬው አንዱ እንጅ፤ የምትለው ኢብቲሳም፤ ኢትዮጵያን እንዴት ብዬ ነው የምገልጻት? እናትን መግለጽ ይቻላል? እናትን መግለጽ ከተቻለ ኢትዮጵያን በዚያ ልክ መግለጽ ይቻል ይሆናል፤ እኔ ግን አይቻለኝም በማለት ትናገራለች። “የዛሬ 11 ዓመት ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጣሁት፤ የሰው ፊት አልገረፈኝም፤ ፊቱን ያዞረብኝም የለም። ኢትዮጵያውያን ደግ፣ ቅንና ደስ የምትሉ ሕዝቦች ናችሁ” ስትል ስሜቷን ትገልጻለች። ኢትዮጵያ እንደ ኒውዮርክ እያደገች ነው፤ እኛ ከመጣን በኋላ እንኳን በርካታ ለውጦች ዕያየን ነው ስትልም የኢትዮጵያን የለውጥ ሂደት አንስታለች። ለአብነትም ባለፉት ሁለት ዓመታት ብቻ በርካታ ነገሮች መስተካከላቸውን በመጠቆም፤ ለዚህም የኢትዮጵያን መንግሥት እናመሠግናለን ብላለች። ከፍልሰተኞች ጋር በተያያዘ በርካታ ሕጎች በመሻሻላቸው፤ ዛሬ በራሴ ስም ንግድ ፈቃድ አውጥቼ እየሠራሁ ነው፤ በጨረታዎችም እወዳደራለሁ፤ የበጎ አድራጎት ማኅበር መመሥረትና መምራት ችያለሁ። እነዚህ ሁሉ የኢትዮጵያ መንግሥት ያመጣቸው ለውጦች ናቸው ብላለች። በምድረ ኢትዮጵያ ያለን ሁሉ ለኢትዮጵያ ዕድገት እንተባበር ስትልም ጥሪ አቅርባለች። ህልማችን ከኢትዮጵያውያን ጎን ሆነን ኢትዮጵያን በማሳደግ ጥረት በንቃት መሳተፍ ነው፤ የኢትዮጵያን እና ሕዝቧን ውለታ መመለስ አለብን ስትልም ትናገራለች። በኢብቲሳም ኻሊድ ቤት በተዘጋጀ የኢፍጣር መርሐ-ግብር ላይ የተሳተፈው አነስ አንዋር ለኢዜአ እንዳለው፤ ኢትዮጵያ በሯን ከፍታ አስጠልላዋለች። ከተለያዩ ሀገራት ብንመጣም ሰብሰብ ብለን ስናፈጥር፤ ማኅበራዊና ቤተሰባዊነታችን ይጠናክራል ብሏል። ብዙ ፈተናዎችን ዐይተናል፤ አልፈናቸው እዚህ ደርሰናል የሚለው አነስ፤ “ኢትዮጵያዊነት መልካምነት ነው” ሕዝቡ በክብር ነው የተቀበለን፤ ከምሥጋና ውጭ ምን ማለት እንችላለን? አመሥጋኞች ነን ሲል ገልጿል። እየተማርኩ ነው፤ ትምህርቴን አጠናቅቄ በሙያዬ በመሠማራት ኢትዮጵያን ማገዝ እፈልጋለሁ ብሏል። ራኪያ አሊ አብዱረዛቅ በበኩሏ በፈረንጆቹ 2011 ወደ ኢትዮጵያ መምጣቷን ታወሳለች። ትምህርቷንም ተከታትላ መመረቋን ገልጻ፤ ቤተሰብ አፍርታ ሁለት ልጆችንም ወልዳ እየኖረች ነው። ኢትዮጵያ ሁለተኛ ሀገሬ ናት፤ ሰላም አላት፤ ሕዝቡም ሰው አክባሪ ነው። ለኢትዮጵያ የተሻለ ልማት ደግሞ መተባበር ወሳኝ ስለሆነ ለዚሁ እንትጋ ስትል መልዕክቷን አስተላልፋለች። #ፍልሰተኞች #ኢዜአ
ከዛፍ የሚታለብ ወተት
Feb 27, 2026 732
በቀደሰ ተክሌ -(ከሚዛን አማን ቅርንጫፍ) ጥበብ ከተፈጥሮ ጋር ስትገናኝ ሌላ እውነት ሌላ አዲስ ነገር ትፈጥራለች። የሰው ልጅ የመመራመርና የማወቅ ተፈጥሯዊ ባህርይው በተፈጥሮ ላይ ሁሉን የማድረግ ሥልጣንን ያስቸረ ነው። ሰው ያልነበረን አዲስ ነገር መፍጠር ባይችልም፤ ከነበረው ሌላ ውጤት ማግኘት ወይም መፍጠር ይችላል። "ጉማታ" በረከትን የመጋራት እሴት!! በዓለማችን ሰውን እና እቃን ከቦታ ወደ ቦታ የማንቀሳቀስ ትልቅ አገልግሎት ያለው ተሽከርካሪ ሕይወት ያለው መስሎ እንዲታይ የሚያደርገው የተገጠመለት ጎማ ነው። ታዲያ ይህ ጎማ ከዛፍ በተገኘ የወተት ጠብታ የሚሰራ መሆኑ አግራሞትን ከሚፈጥሩ የጥበብ ሥራ ውጤቶች መካከል እንዲሆን ያደርገዋል። የጎማ መስሪያ የሆነው ጥሬ ምርት ከዛፍ እንዴት እንደሚዘጋጅ ከስፍራው ኢዜአ የተመለከተውን ሊያስቃኛችሁ እነሆ ይላል፡- በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የጎማ ዛፍ ልማት በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ቤንች ሸኮ ዞን ጉራ ፈርዳ ወረዳ ይገኛል። በምስራቅ አፍሪካ ብቸኛ የተባለው ይህ የጎማ ዛፍ ልማት በ3 ሺህ 884 ሔክታር መሬት ላይ ያረፈ ነው። አረንጓዴ ካባ የደረበውን የበበቃ ቀዬ እንደተሻገሩ ቀጥ ቀጥ ብለው የቆሙ ዛፎች ቅርንጫፋቸውን ከመሬት ከፍ አድርገው ግንዱን ለሌላ ተግባር እየተዉ አድገው በአዲስ ብርሃን ቀበሌ ደምቀው ይታያሉ።   እነዚህ ዛፎች ከወገብ በታች ባለው ክፍል ብዙ ሺህ ጅራፍ እንዳረፈበት ገላ ሰምበር በሰንበር ሆነዋል። ይህም ሌሊት ሌሊት በሚፈጸም ከዛፉ ወተት ለማምረት በተደረገ ጥረት ሳቢያ የተፈጠረ ነው። ጎማን ለመሥራት የሚያስችለውና ከዛፉ የሚገኘውን ወተት ማምረትም የሰለጠኑ ባለሙያዎች ሌሊት ከ9 ሰዓት ጀምሮ የሚከውኑት ተግባር ነው። ይህን ሥራ ለማቀላጠፍም ከ500 በላይ የሚሆኑ ሰራተኞች ላይና ታች ይላሉ። ሠራተኞቹም ራሳቸውን ከማስተዳደር ባለፈ በወዝ በላባቸው ለሀገር አዎንታዊ ተጠቃሚነት የሚውለውን ምርት ያቀርባሉ። የጎማ ዛፍ በተፈጥሮ ብዙ ወተት የሚይዘው ሌሊት ነው። ቀን የሰበሰበውን ወተት ሌሊት ያለ ስስት ይለግሳል። በዚህን ሰዓት ዛፉን አድምተው ወተት ሊያልቡ የተዘጋጁ ሠራተኞች በሰለጠኑት ሙያ መሠረት የፀሐይ መውጫና መግቢያ አቅጣጫን ቀድመው ይለያሉ። የፀሐዩን አቅጣጫ ከለዩ በኋላ በዛፉ ሰሜንና ደቡብ አቅጣጫ ጎን ላይ በስለታማ ቁስ በአንድ መስመር ቀጥ አድርገው በመፈቅፈቅ ለዛፉ ወተት መውረጃ ቦይ ያበጃሉ። በመቀጠል ሁለቱን መስመሮች ከፊት ለፊት የሚያገናኝ ሌላ መስመር በማበጀት የዛፉ ወተት መሰል ፈሳሽ ከስር ወደተቀመጠው ፈሳሽ መቀበያ ባልዲ ያለ ስስት ይፈሳል።   የጎማ ዛፍ ወተት ጠብታ ከእያንዳንዱ ዛፍ ስር ተሰብስቦ በብዙ ሊትር ተመዝኖ በበርሜል ይከማቻል። በአግባቡ የማጣራትና አሲድ ጨምሮ የማርጋት ሥራ ወደ ሚሰራበት ክፍል ይገባል። ወተቱ ከረጋ በኋላም ይታጠባል። ተድጦ የሚፈለገውን ያህል ቅርጽ ከያዘ በኋላ ጋቢ መስሎ ፀሐይ ላይ ይሰጣል።   በፀሐይ ኃይል ጠፈፍ እንዲል የተሰጣው ምርት የተያዘለት ሰዓት ሲጠናቀቅ በባህላዊ መንገድ ወደ ተዘጋጀው ጭስ ቤት ይላካል። በዚህ ክፍል ውስጥ ለዚሁ ተግባር የሚያገለግሉ በተለያየ ደረጃ የተዘጋጁ እሳት ማንደጃ ጉድጓዶች ይገኛሉ። ከፀሐይ ላይ ተሰጥቶ ወደ ውስጥ እንዲገባ የተደረገው ምርት በዚህ ክፍል ከ5 እስከ 6 ቀናት የተለያዩ የድርቀት ደረጃዎችን እየተሸጋገረ ይቆያል። በጥሩ ሁኔታ ቀይ ሆኖ ከደረቀ በኋላ ለጎማ ኢንዱስትሪ ጥሬ ዕቃ ሆኖ ለሽያጭ ዝግጁ ይሆናል።   ሁለት አስርተ ዓመታትን ያስቆጠረው የጎማ ልማትና ምርት ሥራ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባውን የጎማ ጥሬ ዕቃ በከፊል በመሸፈን በሀገራዊ ኢኮኖሚው ላይ የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። በኬሚካል ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን የጎማ ዛፍ ልማትና ምርት ፕሮጀክቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘማች ሳድንስ እንደሚሉት፤ የጎማ ዛፍ አንድ ጊዜ ከተተከለ በኋላ ዓመቱን ሙሉ ምርት የሚሰጥ ዛፍ ነው። የወተት ምርት ለመስጠት ችግኙ ከተተከለ በኋላ ለሦስት ዓመታት ይቆያል።   በጉራፈርዳ ወረዳ ለምቶ ምርት እየሰጠ ካለው ዛፍ በወር ከ37 እስከ 40 ቶን የጎማ ዛፍ ጥሬ ምርት በመመረት ላይ ሲሆን ዘንድሮ ከ560 ቶን በላይ ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ በማቅረብ የዘርፉን የጥሬ ምርት ፍላጎት በከፊል ለመመለስ እየተሰራ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ከ87 ሺህ ሄክታር በላይ ለጎማ ዛፍ ምቹ መሬት እንዳላት ጥናቶች ያመለክታሉ። ይሁን እንጂ በስፋት ወደዚህ ዘርፍ በመግባት የዘርፉን ኢኮኖሚ መጠቀም አልተቻለም። የኬሚካል ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን የጎማ ዛፍ ልማትን ለማስፋፋት አቅዶ በጥናት ከተለዩ ቦታዎች መካከል በኦሮሚያ ክልል ኢሉአባቡር ዞን ከ2 ሺህ 500 ሔክታር በላይ መሬት ተረክቦ ችግኝ የማዘጋጀት ተግባር እያከናወነ ይገኛል። በዚህም የሀገር ውስጥ የጥሬ ምርት ፍላጎትን በሀገር ውስጥ በመሸፈን እና የተረፈውን ኤክስፖርት በማድረግ ከዘርፉ የውጭ ምንዛሬ ማግኘት የሚቻልበትን ዕድል ለመፍጠር ትኩረት መደረጉን አቶ ዘማች ጠቁመዋል። ባለሃብቶች ወደዚህ ዘርፍ ቢሰማሩ ሀገርን የሚጠቅሙ ውጤቶችን ማምጣት እንደሚቻልም አክለዋል። ኢትዮጵያ በየዘርፉ ያላት የኢኮኖሚ አቅም የዕድገት ጉዞዋ አቅሞች ናቸው። በተለይ ለም አፈሯ ከፍተኛ ፋይዳ ያላቸው ምርቶችን በማብቀል ለሀገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን ለዓለም ሀብት መፍጠር የሚያስችሉ መሆናቸውን በብዙ መንገድ ማረጋገጥ እየተቻለ ነው። ብዙም ትኩረት ያልተሰጠው የጎማ ዛፍ ልማትም ከእነዚህ አቅሞች አንዱ ነው። ያሉንን ጸጋዎች ለይቶ ለማልማትና ምርታማነትን ለመጨመር መንግሥት የሰጠውን ትኩረት መሠረት በማድረግ የጎማ ዛፍ ምቹ አጋጣሚዎችን ለይቶ መሥራት ከተቻለ ከዘርፉ በብዙ መጠቀም ይቻላል፡፡
ሶስት አስርት ዓመታትን የተሻገረው የኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ወዳጅነት
Feb 26, 2026 608
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በአዘርባጃን ሪፐብሊክ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ዛሬ ማድረግ ጀምረዋል። ይህ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የአዘርባጃን ሪፐብሊክ ጉብኝት የሁለቱን ሀገራት የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጠናከር ማሳያ ነው። ይህ ጉብኝት የሁለትዮሽ ግንኙነቶችን የላቀ እና ትርጉም ያለው ደረጃ ያደርሰዋል።   ኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የጀመሩት አዘርባጃን እ.አ.አ በ1991 ነጻነቷን ማግኘቷን ተከትሎ ነው። የሀገራቱ ግንኙነት ከእ.አ.አ 1990ዎች መግቢያ አንስቶ እያደገ መጥቷል። አዘርባጃን እ.አ.አ በ2015 በኢትዮጵያ ኤምባሲ የከፈተች ሲሆን ይህም የሁለቱን ሀገራት የዲፕሎማሲ ትብብር እንዲጠናከር በር ከፍቷል። በቱርክዬ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ኢትዮጵያ ከአዘርባጃን ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ስራ የሚሸፍን ሲሆን ፖለቲካ፣ ትምህርት እና ባህል ሀገራቱ ካላቸው የትብብር መስኮች መካከል ተጠቃሽ ናቸው።   የሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እየጎለበተ መምጣቱን ከሚያመላክቱ ጉዳዮች መካከል በባለብዙ ወገን መድረክ በገለልተኛ ሀገራት ንቅናቄ (ናም) መድረክ በትብብር እየሰሩ መገኘታቸው ተጠቃሽ ነው። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2019 በአዘርባጃን ባኩ በተካሄደው 18ኛው የገለልተኛ ሃገራት ንቅናቄ (ናም) ጉባኤ ላይ ተሳትፋለች። የገለልተኛ ሀገራት ንቅናቄ 120 አባል ሃገራትን ያቀፈና ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቀጥሎ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የዓለም ሀገራትን በአባልነት የያዘ ስብስብ ነው። የኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ወዳጅነት የደቡብ ደቡብ ትብብር ማሳያ ተደርጎም ይወሰዳል። በሀገራቱ መካከል ተከታታይ የሆኑ የባህል ልውውጥ መድረኮች ተካሄደዋል። ለዚህም እ.አ.አ በ1960ዎቹ የኢትዮጵያ ተማሪዎች በአዘርባጃን የትምህርት እድል አግኝተው ይከታተሉ እንደነበር መረጃዎች ያሳያሉ። ከኢኮኖሚ አንጻር እ.አ.አ በ2017 በአዘርባጃን የተካሄደው የሁለቱ ሀገራት የቢዝነስ ፎረም ተጠቃሽ ነው። በወቅቱ ጨርቃጨርቅን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ የኢትዮጵያ የንግድ ማህበረሰብ አባላት ተሳትፈዋል። በወቅቱ ሀገራቱ እርስ በእርስ ያላቸውን የንግድ ልውውጥ ምጣኔ ለማሳደግ የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ባለስልጣናት መካከል የሚደረጉ የጉብኝት ልውውጦች እያደጉ መጥተዋል።   ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በግንቦት ወር 2016 ዓ.ም በአዘርባጃን ጉብኝት ማድረጋቸወ ይታወሳል። ኢትዮጵያና አዘርባጃን በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በቴክኖሎጂና በሌሎች ዘርፎች ያላቸውን ትብብር የበለጠ ማሳደግና በጋራ መስራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ዙሪያ መምከራቸውም እንዲሁ። ምክክሩ እጅግ ውጤታማ የነበረ ሲሆን የሁለቱን ሀገራት ህዝብ ዕድገት እና ብልፅግና በመደጋገፍና በትብብር መንፈስ ለመስራት ስምምነት ላይ መድረሳቸውም በወቅቱ ተገልጿል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ከአዘርባጃን የሀገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስትር ኮሎኔል-ጀነራል ኢይቫዞቭ ቪላያት ሱለይማን ጋር በነበራቸው ውይይት የደህንነት ጉዳዮችን ጨምሮ የኢትዮጵያን እና አዘርባጃን የሁለትዮሽና የባለብዙ ወገን ትብብሮችን ማጠናከር የሚያስችሉ ቀጣይ ስራዎች ላይ መክረዋል። በውይይቱም በመረጃ፣ በፀጥታና ደህንነት ዘርፎች የጋራ ትብብር አቅም ግንባታና ሌሎች ጉዳዮች ሁለቱን ሀገራት ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን በጋራ ለመፈጸም መስማማታቸውን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ መግለጻቸው ይታወሳል።   እ.አ.አ በ2017 በወቅቱ የአዘርባጃን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩት ኤልማር ማማድያሮቭ በኢትዮጵያ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸውና የኢትዮጵያ እና አዘርባጃን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች በቋሚነት የፖለቲካ ምክክር ማድረግ የሚያስችላቸውን የጋራ መግባቢያ ስምምነት መፈራረማቸው ይታወቃል። የአዘርባጃን የፐብሊክ ሰርቪስ እና ማኅበራዊ ፈጠራ ተቋም ሊቀ መንበር ኦልቪ ሜዲዬቭ የብሔራዊ ቤተመንግሥት እና የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎትን በሰኔ ወር 2017 ዓ.ም ጎብኝተዋል። ኦልቪ ሜዲዬቭ በወቅቱ ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ጋር ተወያይተዋል።   የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ(ዶ/ር) በጥር ወር 2017 ዓ.ም በአዘርባጃን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ያልቺን ራፊየቭ የተመራ ልዑክ ጋር በአዲስ አበባ ተወያይተዋል፡፡ በውይይታቸውም ኢትዮጵያ ወደ አዘርባጃን የምትልካቸው ምርቶች ብዝኀነትን ለማሳደግና ለማስፋፋት ቁርጠኛ መሆኗን ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ(ዶ/ር) ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያ ወደ አዘርባጃን ከምትልካቸው ምርቶች መካከል ሰሊጥ፣ የተቆላ ቡና፣ ተልባ፣ የፍየል እና የበግ ሥጋን ጨምሮ ሌሎች ምርቶች እንደሚገኙበት ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡   በአዘርባጃን የመከላከያ ኢንዱስትሪ ሚኒስትር ቩጋር ሙስታፋይ የተመራ ልዑክ በህዳር ወር 2018 ዓ.ም በኢትዮጵያ ከመከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሀመድና ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አካሂዷል፡፡ በውይይቱ ኢትዮጵያ እና አዘርባጃን በመከላከያ ዘርፍ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር መስማማታቸው ይታወሳል። በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካና ንግድ ትብብር ላይ ያተኮረው ሶስተኛ የኢትዮ-አዘርባጃን የውይይት መድረክ በጥር ወር 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ተካሂዷል። ከውይይቱ በኋላ ሀገራቱ የኢኮኖሚ እና የንግድ ግንኙነታቸውን ለማሳደግና ተጨማሪ እድሎችን መፈተሽ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይም መግባባት ላይ ደርሰዋል። 29ኛው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 29) በህዳር ወር 2017 ዓ.ም በአዘርባጃን መካሄዱ ይታወቃል። በጉባኤው ኢትዮጵያ በፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በተመራ ልዑክ ተሳትፎ አድርጋለች። በወቅቱ የኢትዮጵያ ልዑክ ከአዘርባጃን ባለስልጣናት ጋር በመወያየት ሀገራቱ በአካባቢ ጥበቃ፣ አየር ንብረት ለውጥ መከላከል እና አረንጓዴ ልማት ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር በቁርጠኝነት ለመስራት የጋራ መግባባት ላይ ደርሰዋል። በሀገራቱ መካከል ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የተደረጉ ውይይቶችና የልምድ ልውውጦች የሁለትዮሽ ዲፕሎማሲያዊ ትብብር እየጠነከረ መምጣቱን ያሳያል። ኢትዮጵያ እና አዘርባጃን በንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ግብርና፣ ዲጂታላይዜሽን፣ ትምህርት እና ባህልን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች ትብብራቸውን ለማጠናከር ይሻሉ።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በአዘርባጃን ሪፐብሊክ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ዛሬ ማድረግ መጀመራቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። የኢትዮጵያ እና የአዘርባጃን ግንኙነት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየጠነከረ መምጣቱን የገለጸው ጽህፈት ቤቱ ለዚህም ጉልህ ማሳያው በጠንካራ ትብብር የቀጠለው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ጎልቶ እንደሚታይ አንስቷል። የዛሬው የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የአዘርባጃን ሪፐብሊክ ጉብኝትም የዚሁ የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጠናከር ማሳያ መሆኑን ጠቁሟል። ይህ ጉብኝት የሁለትዮሽ ግንኙነቶችን የላቀ እና ትርጉም ያለው ደረጃ እንደሚያደርስ ይጠበቃል ሲልም ጽህፈት ቤቱ አመልክቷል። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጉብኝት በመሪ ደረጃ የሚደረግ መሆኑ በሁለቱ ሀገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ውስጥ ትልቅ ትርጉም ይሰጠዋል። ሶስት አስርት ዓመታትን የተሻገረው የኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በሁለትዮሽ፣ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚሸጋገር የቅርብ ዓመታት ውይይቶች እና ጉብኝቶች ማሳያ ናቸው።
የኢትዮጵያ የስኬት ጉዞ …
Feb 26, 2026 360
(በሙሴ መለሰ) ኢትዮጵያ በየዘርፉ እያስመዘገበቻቸው የሚገኙት ስኬቶች በተለያዩ የዓለም መድረኮች በምሳሌነት እያስጠቀሳት ይገኛሉ። ኢትዮጵያ በአምስቱ ዋና ዋና የኢኮኖሚ አምዶቿ ማለትም በግብርና፣ በኢንዳስትሪ፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም እና በቴክኖሎጂ ዘርፎች እየተመዘገቡ የሚገኙ ስኬቶችን ቀጥለን እንዳሥሣለን። የስንዴ ምርታማነት ስኬት ኢትዮጵያ በግብርና በተለይ በሌማት ትሩፋት እና በስንዴ ልማት ምርታማነትን በከፍተኛ ደረጃ ስኬት ያስመዘገበችባቸው መስኮች ናቸው። ቀደም ሲል ስንዴን ከውጭ ለማስገባት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ታወጣ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ። ከለውጡ መንግስት ወዲህ ግን በተለይ ለስንዴ ልማት በተሰጠው ከፍተኛ ትኩረት የግብርና ሜካናይዜሽን በመጠቀም ምርት እና ምርታማነትን በከፍተኛ መጠን ማሳደግ በመቻሉ ከራስ ፍላጎት ባለፈ ለውጭ ገበያ በማቅረብ ላይ ትገኛለች። ይህ ውጤታማነቷም በተለያዩ የዓለም ዓቀፍ ተቋማት ጭምር እውቅና አስችሯታል። ለስንዴ ምርት እና ምርታማነት ማደግ ዘመናዊ የመስኖ ሥርዓቶች፣ የኩታ ገጠም አስተራረስ ዜዴ፣ የግብርና ሜካናይዜሽን ስልቶችና የግብርና ኢኒሼቲቮች በዋና ምክንያትነት ይጠቀሳሉ። በዚህ መነሻነት ነው የአፍሪካ ኅብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽን ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ የኢትዮጵያ የስንዴ ምርታማነት ለአፍሪካ አርዓያነት ያለው መሆኑንና በስንዴ ልማት ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ያስመዘገበችው ለውጥ ከፍተኛ መነሳሳት መፍጠሩን ጠቅሰዋል። ይህን የኢትዮጵያን ውጤታማነት መነሻ በማድረግም የአፍሪካ ሀገራት እንዲተገብሩት መክረዋል። በተመሳሳይ በ2016 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተባበሩት መንግሥታት የምግብ እና የእርሻ ድርጅት የከበረውን የፋኦ አግሪኮላ ሜዳሊያ መሸለማቸው ይታወቃል። ሽልማቱ በምግብ ዋስትናና በተመጣጠነ የምግብ አቅርቦት ላሳዩት ትጋት፣ ፈጣን፣ ተለዋዋጭና ፈታኝ በሆነው ከባቢያዊ ሁኔታ በስንዴ ምርት ራስን ለመቻል በተከተሉት ፈጠራዊ መፍትሔ ዕውቅና ለመስጠት የተበረከተ ነው። የኢትዮጵያ የስንዴ ምርታማነት ስኬት የግብርናው አብዮት ማሳያ ሲሆን፤ ራስን መቻል እና ለአፍሪካ መብቃትን ያለመ ነው። ዲፕሎማሲያዊ ስኬት   በሰላም ግንባታ፣ ግጭት አፈታት እና አኅጉራዊ ትሥሥር ረገድ ሚናዋን እየተወጣች ያለችው ኢትዮጵያ፤ በዲፕሎማሲው መድረክም ተደማጭነቷ እያደገ መጥቷል። በሰላም ማስከበር፣ አረንጓዴ ዐሻራና በሌሎች ዐበይት ጉዳዮች ኢትዮጵያ በቅርብ ጊዜያት በዓለም መድረኮች ስሟ ከፍ ብሎ እየተሰማ ነው።   የቱርክዬ ፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን፣ የሕንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ የኬንያ ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ፣ የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ይ፣ የአሜሪካ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክርስቶፈር ላንዳው፣ የእስራኤል ፕሬዚዳንት አይዛክ ሄርዞግ እና የሌሎች ሀገራት ባልሥልጣናት የቅርብ ጊዜ የኢትዮጵያ ጉብኝቶች የሀገሪቱን የጂኦ ፖለቲካዊ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ብሎም የዲፕሎማሲ ተደማጭነት እያደገ መምጣት ያሳያሉ። ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲው መስክ ብሔራዊ ጥቅሟን ከማስጠበቅ ባለፈ በዓለም መድረክ የአፍሪካ ድምጽ እየሆነች ትገኛለች።   አረንጓዴ ዐሻራ - ሌላኛው የኢትዮጵያ ስኬት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት በሀገር አቀፍ ደረጃ ሐምሌ 2011 ዓ.ም በተጀመረው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር፤ እስከአሁን ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞች ተተክለዋል። በ2011 ዓ.ም 17 ነጥብ 2 በመቶ የነበረው የኢትዮጵያ የደን ሽፋን፤ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት በአረንጓዴ ዐሻራ በተከናወነው ሥራ አሁን ላይ ከ23 በመቶ በላይ ደርሷል። በኢትዮጵያ በተካሄደው 2ኛው የዓለም የምግብ ሥርዓት ጉባዔ የአረንጓዴ ዐሻራ ሥራው ዕውቅና ተችሮታል። በተጨማሪም በ2ኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባዔ የአረንጓዴ ዐሻራ ሥራዋን ኢትዮጵያ ባስተዋወቀችበት ወቅት፤ የአፍሪካ ሀገራት ትልቅ ተምሳሌት የሚሆን ኢኒሼቲቭ መሆኑንም በምሳሌነት ጠቅሰውታል። ኢትዮጵያ ለጎረቤቶቿ ችግኝ በመስጠት የአካባቢ ጥበቃ የጋራ አጀንዳ መሆኑን አሳይታለች። ይህም "አረንጓዴ ዲፕሎማሲ" በመባል የሚታወቅ ሲሆን፤ በሀገራት መካከል በጎ ግንኙነትን ለማዳበር አስተዋጽኦ አበርክቷል።   የግዙፍ (ሜጋ) ፕሮጀክቶች ግንባታና ምረቃ በወርሃ ጳጉሜን 2017 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተመረቀው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለአፍሪካ የኢነርጂ ትሥሥር ውጥን ትልቅ የምሥራች ነው። የጎረቤት ሀገራት ከኢትዮጵያ የሚያገኙት የኤሌክትሪክ ሀይል አቅርቦትም ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከር ያስችላል። በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙ የሀገራት መሪዎች ባደረጉት ንግግር የሕዳሴ ግድብ የአፍሪካ ራስን የመቻል ምልክት እና የኢትዮጵያ አይበገሬነት ተምሳሌት መሆኑን በአጽንኦት አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፤ የኒውክሌር ማበልጸጊያ እንደሚገነባ፣ የጋዝ ፋብሪካ እንደሚመረቅ፣ የነዳጅ ማጣሪያ ዕውን እንደሚሆን፣ በአፍሪካ ግዙፍ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እንደሚገነባ፣ የማዳበሪያ ፋብሪካን ጨምሮ የ1 ነጥብ 5 ሚሊየን ቤቶች ግንባታ እንደሚከናወን ጉባ ላይ ማብሠራቸው ይታወሳል።   ይህን ተከትሎም በሶማሌ ክልል የጋዝ ፋብሪካ ተመርቋል፣ የቢሾፍቱ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታም ተጀምሯል። የሌሎች መሠረተ ልማቶች ግንባታ እና የዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛል። እየተገነባ ያለው ኮይሻ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫም ለኢነርጂ አቅርቦት ዕድገት የበኩሉን ሚና እንደሚጫወት መገለጹ ይታወሳል።   የኮሪደር ልማት እና የከተማ ማዘመን ሥራዎች የኮሪደር ልማት ኢኒሼቲቮች የትራንስፖርትን ጨምሮ የተለያዩ መሠረተ ልማቶች እንዲዘምኑ፣ የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች እንዲስፋፉ፣ የንግድ ተቋማት አሰራር እንዲዘምን፣ አምፊ ቴአትርን ጨምሮ የኪነ-ጥበብ መሠረተ ልማቶች እንዲገነቡ፣ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ግንባታ እንዲከናወን የራሳቸውን አስተዋጽኦ አበርክተዋል። የኮሪደር ልማቱ አዲስ አበባን ጨምሮ በርካታ የክልል ከተሞችን ከማስዋብ ባለፈ ዜጎች በንጹህ አካባቢ እንዲኖሩ አስችሏል። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት(አይ ኤም ኤፍ) ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክሪስታሊና ጆርጂዬቫ እ.አ.አ በ2025 ስለ አዲስ አበባ ሲናገሩ፤ ከተማዋን ጊዜ ወስደው መመልከታቸውንና ከፍተኛ መሻሻል እንዳዩ መግለጻቸው አንዱ ማሳያ ነው። የኬንያ የፓርላማ አባል ጁኔት መሐመድም አዲስ አበባን የአፍሪካ አዲሷ ዱባይ ሲሉ አድንቀው፤ አዲስ አበባ እያስመዘገበች ያለው ፈጣን ዕድገት ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ምሳሌ መሆኑንም ገልጸዋል። በተጨማሪም የተለያዩ ዲፕሎማቶች፣ የውጭ ሀገር ዜጎች እንዲሁም የልማት አጋሮች ለአዲስ አበባ የከተማ መዘመንና ለውጥ ምስክርነታቸውን መስጠታቸው አይዘነጋም።   በሰው ሠራሽ አስተውሎት ረገድ ኢትዮጵያ ለቴክኖሎጂና ሰው ሠራሽ አስተውሎት ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ከአምስት ዓመታት በፊት የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትን አቋቁማ ወደ ሥራ ገብታለች። በዘርፉ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪ ትምህርት እየተሰጠም ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓልን አስመልክቶ ባካሄደው መድረክ ላይ፤ ፈጥነን ልጆቻችንን ካዘጋጀን ሰው ሠራሽ አስተውሎትን እንደ ተለያዩ ምርቶች በቀላሉ መጠቀም እንችላለን ሲሉ አጽንኦት ሰጥተዋል። ለሰው ሠራሽ አስተውሎት ፖሊሲ እና ስትራቴጂ ተዘጋጅቶ እየተተገበረ መሆኑን ገልጸው፤ ኢትዮጵያ የምትገነባው የኤ አይ ዩኒቨርሲቲም የኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ብዙ ችግሮችን ይፈታል ብለዋል። ኢትዮጵያ ለሰው ሠራሽ አስተውሎት መሠረት እየጣለች መሆኗንም አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ ዘመኑን የዋጀ ዕይታ ለዲጂታል ዘመን ለውጦች ምላሽ ከመስጠት ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትንም ይፈጥራል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ እና የኢትዮጵያ ሰው ሠራሽ አስተውሎት ኢንስቲትዩት ኢትዮጵያን በዲጂታል ዘርፉ ወደ ቀጣይ ምዕራፍ የማሸጋገር ዐቅም አላቸው።   ኢትዮጵያ - የአፍሪካ የአቪዬሽን ማዕከል የአፍሪካ አቪዬሽን ምልክት የሆነው ግዙፉ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፤ ኢትዮጵያን ከቀሪው ዓለም እና አፍሪካን ርስ በርስ በማገናኘት በኩል የመሪነት ሚናውን እየተወጣ ነው። የአየር መንገዱ የመንገደኞች እና የካርጎ አገልግሎቶች የንግድ፣ የቱሪዝም እና ዓለምአቀፍ የቢዝነስ ግንኙነቶች እንዲጠናከሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተም ይገኛል። በተያዝው በጀት ዓመት የመጀመሪያ አጋማሽም አየር መንገዱ 10 ነጥብ 64 ሚሊየን ሰዎችን ማጓጓዝ መቻሉ ለመሪነቱ ትልቅ ማሳያ ሆኖ ይወሰዳል። በሌላ በኩል በአፍሪካ ግዙፍ የሆነው ቢሾፍቱ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ተጀምሯል። የዚህ ግንባታ መጀመር ኢትዮጵያ በአፍሪካ አቪዬሽን ያላትን የመሪነት ሚና አጠናክሮ ለማስቀጠል ሁነኛ ሚና አለው።   ሌላኛው የኢትዮጵያ ስኬት - ቱሪዝም ኢትዮጵያ በታሪክ፣ ባህል፣ በተፈጥሯዊ እና ሰው ሠራሽ የቱሪዝም መዳረሻዎች የታደለች ናት። እነዚህም ጎብኚዎችንና ተመራማሪዎችን መሳባቸውን ቀጥለዋል። መንግሥት እንደ አንድ የኢኮኖሚ ምሰሶ ወስዶ እየሠራበት በሚገኘው የቱሪዝም ዘርፍ በተከናወኑ ሥራዎች አበረታች ውጤቶች ተገኝተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት፤ በገበታ ለሸገር፣ በገበታ ለሀገር እና በገበታ ለትውልድ አማካኝነት የተከናወኑ ሥራዎች የቱሪዝም ፀጋን ከመግለጥ ባለፈ የገቢ መጠንን እያሳደጉም ይገኛሉ። በቅርቡ በሶማሌ ክልል የተመረቀው እና የገበታ ለትውልድ ሥራ አካል የሆነው የሸበሌ ሪዞርት የዚሁ ሥራ ማሳያ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በምረቃው ወቅት፤ ሪዞርቱ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ የገባነውን ቃል በተግባር ያረጋገጠ የምሥራቁ የሀገራችን ክፍል ትልቅ ሥራ ነው ማለታቸው ይታወሳል። በአዲስ አበባ የሚገኙት የወዳጅነት ዐደባባይ፣ አንድነት ፓርክ፣ ሳይንስ ሙዚየም እና ሌሎችም ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻዎች ሆነዋል። የኮሪደር ልማቱም የመዲናዋን መልክ በአዲስ ሁኔታ በመግለጥ ጎብኚዎችን እየሳበ ነው። በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በግብርና፣ በዲፕሎማሲ፣ በኢኖቬሽን፣ በመሠረተ ልማት፣ በከተማ ማዘመንና ኮሪደር ልማት፣ ቱሪዝምን ጨምሮ በሌሎች መስኮች ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች የራሷን መጻኢ ጊዜ ብሩኅነት ያመላክታሉ። የኢትዮጵያ ስኬቶች ብሎም ስትራቴጂካዊ ራዕይ ጊዜውን የሚመጥን ዕድገትን በትጋትና በጋራ ትብብር የመሥራት ውጤትን የሚያሳዩ ናቸው። ኢትዮጵያ ለዛሬ ብቻ እየሠራች አይደለም፤ ቀጣይ ለሚመጡ ትውልዶች መሠረት እየጣለችም እንጂ።
የኢትዮጵያ ዐሻራ ከዓድዋ - እስከ አፍሪካ ኅብረት
Feb 14, 2026 615
በሙሴ መለሰ ኢትዮጵያ በአፍሪካ የፖለቲካ፣ የታሪክ እና ዲፕሎማሲ ምኅዳር ውስጥ ልዩ ስፍራ እና ተጽዕኖ ያላት ሀገር ናት። የጥንታዊ ሥልጣኔዎች ባለቤት የሆነችው ኢትዮጵያ፤ በቅኝ ያልተገዛች ብቸኛ የአፍሪካ ሀገር ከመሆኗ ባሻገር ለፓን አፍሪካኒዝም ንቅናቄ መስፋፋት ትልቅ ሚና ተጫውታለች። ይህንም ታሪክ ይዘክራል። 39ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባዔ ዛሬ ይጀመራል አይበገሬነት፣ ሉዓላዊነት እና የፓን አፍሪካ መንፈስ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ውስጥ ካሳረፈቻቸው ዐሻራዎች መካከል በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ። በዘመናዊው ዓለምም በአፍሪካ አጀንዳዎች ላይ ወሳኝ ሚና እየተጫወተች ትገኛለች። ኢትዮጵያ የአፍሪካ የነጻነት እና ማንነት ተምሳሌት ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1896 በዓድዋ ጦርነት በጣሊያን ኃይሎች ላይ የተቀዳጀችው ድል በአፍሪካ እና በጥቁር ሕዝቦች ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ቦታ የሚሰጠው ነው።   አብዛኛው የአፍሪካ አኅጉር በቅኝ ግዛት ውስጥ በነበረበት ወቅት ኢትዮጵያ ያስመዘገበችው ድል ሉዓላዊነቷን ከማስጠበቅ ባለፈ በአፍሪካ እና በአፍሪካ ዳያስፖራ የነጻነት ትግሎች እንዲቀጣጠሉ አድርጓል። በተለይም ከ20ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ ለነበሩ እንቅስቃሴዎች ወሳኝ ሚና ተጫውቷል። ይህ ታሪካዊ ዐሻራ ኢትዮጵያን የጥቁሮች ኩራት፣ ትግል እና ራስን የመቻል ምልክት እንድትሆን አስችሏታል። የአፍሪካ የዲፕሎማሲ መዲና አዲስ አበባ የአፍሪካ ኅብረት ዋና መቀመጫ መሆኗ ኢትዮጵያ የአኅጉሪቷ የዲፕሎማሲ ማዕከል ሆና እንድትቀጥል አስችሏል። እ.አ.አ በ1963 የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (የአሁኑ የአፍሪካ ኅብረት) ታሪካዊ ምሥረታ የተካሄደው በኢትዮጵያ ነው። ኢትዮጵያ ከድርጅቱ መሥራች ሀገራት መካከል አንዷ ናት። ይህም የአፍሪካ የጋራ የፖለቲካ ድምጽ እንድትሆን ምክንያት ሆኗል። የአፍሪካ ኅብረት፣ የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ኢሴኤ) እና ዓለም አቀፍ የዲፕሎማሲ ተቋማት የሚገኙባት ኢትዮጵያ፤ በዲፕሎማሲው ምክክር እና ውሳኔ ሰጪነት ውስጥ ያላትን ማዕከላዊ ሚና የበለጠ የሚያጠናክር ነው። የፓን አፍሪካኒዝም ድምጽ ኢትዮጵያ በቅኝ አለመገዛቷ ለፓን አፍሪካኒዝም እንቅስቃሴ ሥር መስደድ ወሳኝ ነው። በፓን አፍሪካኒዝም እሳቤ ለአፍሪካ አንድነት እና የጋራ ምላሽ አጥብቃ ስትሞግትም ቆይታለች። በአፍሪካ ኅብረት እና በተለያዩ መድረኮች ኢትዮጵያ የአፍሪካ ችግሮች በአፍሪካውያን መፈታት አለባቸው የሚለውን እሳቤ ለማስረጽ አበክራ እየሠራች ትገኛለች። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ተኮር መፍትሔዎች ከቃላት ባለፈ በአኅጉራዊ የትሥሥር አጀንዳዎች፣ ሰላም እና ደኅንነት ማዕቀፎች እንዲሁም የፖለቲካ እና ኢኮኖሚ ፈተናዎች እንዲፈቱ ድጋፏን በመስጠት ቁርጠኝነቷን አሳይታለች። የአፍሪካ አኅጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ስምምነትንም በፍጥነት አጽድቃ ወደ ሥራ ማስገባቷ የዚሁ አንድ ማሳያ ነው። ሰላም ማስከበር እና ቀጣናዊ መረጋጋት ኢትዮጵያ በቀጣናዊ ሰላም እና መረጋጋት ስትራቴጂካዊ ሚና እየተወጣች ነው። በዚህም መሠረት ለተባበሩት መንግሥታት እና የአፍሪካ ኅብረት የሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች ከፍተኛ አስተዋጽዖ በማድረግ ከአፍሪካ ሀገራት ቀዳሚውን ድርሻ ትይዛለች።   ሶማሊያ፣ ሱዳን እና ደቡብ ሱዳንን ጨምሮ ግጭት ባለባቸው የአፍሪካ ሀገራት ወታደሮቿን በመላክ ለሰላም እና ደኅንነት ያላትን ሚና በተግባር ገልጣ አሳይታለች። የተባበሩት መንግሥታትም ኢትዮጵያ በሰላም ማስከበር እየተወጣች ላለው ሚና ምሥጋናውን ማቅረቡ ይታወቃል። ኢትዮጵያ በቀጣናው ሀገራት ያሉ ግጭቶች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ የተወጣችው የእርቅ እና የዲፕሎማሲ ሚናም ተጠቃሽ ነው።   የኢኮኖሚ እድገት እና ቀጣናዊ ትሥሥር ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በአፍሪካ ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት እያስመዘገቡ ካሉ ሀገራት መካከል በዋናነት ትጠቀሳለች። በ2017 ዓ.ም ማብቂያ የተመረቀው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እና በግንባታ ላይ የሚገኘው ኮይሻ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ከግዙፍ መሠረተ ልማትነታቸው ባለፈ ቀጣናዊ ትሥሥር በማረጋገጥ ረገድ ወሳኝ ሚና አላቸው። ሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያ ቀጣናዊ የኢነርጂ የስኅበት ማዕከል እንድትሆን አድርጓታል። ኢትዮጵያ ለጎረቤት ሀገራት የምትሸጠው ኢነርጂ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትብብርን የሚያሳልጥ ነው። የኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር መንገድን ጨምሮ የመንገድ መሠረተ ልማቶች እና የኢንዱስትሪ ፓርኮች ኢትዮጵያን የቀጣናዊ ትሥሥር ማዕከል እንድትሆን እያደረጓት ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት እየተከናወነ ያለው አረንጓዴ ዐሻራም፤ ኢትዮጵያን የአረንጓዴ ትብብር እና የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ተምሳሌት ማድረግ ችሏል። በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ አጀንዳ የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች ትገኛለች። የባህል እና የሥልጣኔ አስተዋጽዖ ኢትዮጵያ ጥንታዊ ታሪክ፣ ቱባ ባህል እና ብዝኃነት መገለጫዋ ናቸው። የቋንቋ ብዝኃነት በአፍሪካ ውስጥ ገራገር የዲፕሎማሲ ኃይል (Soft Power) እንዲኖራት አስተዋጽዖ አድርጓል። የኢትዮጵያ የሀገርነት ታሪክ እና የሥልጣኔ ትርክት አፍሪካ ያሏትን ጥልቅ የታሪክ ሥሮች ይበልጥ አጉልቶ የሚያሳይ ነው። የኢትዮጵያ ብዝኃ ማንነቶች፣ ሀገር በቀል ዕውቀቶች እና አስደማሚ የሥነ-ሕንጻ ሥራዎች በአፍሪካ ባህል እና ሥልጣኔ ውስጥ ያላቸው ሚና ትልቅ ነው። ኢትዮጵያ አሁንም በአፍሪካ አንድነት እና መረጋጋት ውስጥ እንደ ቁልፍ ምሰሶ ትታያለች። በአኅጉሪቱ ውስጥ ያላት ድርሻ በታሪክ ሥር የሰደደ እና አሁን ባለው ዘመን በዲፕሎማሲ፣ በሰላም ግንባታ እና ልማት ሥራ በግልጽ ጎልቶ ይታያል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ የፖለቲካ መዲና እንዲሁም የአይበገሬነት እና የነጻነት ምልክት ናት። አፍሪካ አንድነቷን ለማረጋገጥ፣ የተረጋጋ አኅጉር ለመፍጠር እና በራስ ዐቅም ነገሮችን የመከወን ጉዞ ትልም ውስጥ የኢትዮጵያ ድርሻ ቁልፍ ነው።   39ኛው የአፍሪካ ኅብረት ጉባዔ “ዘላቂ የውኃ ኑረትና ንጽህና ሥርዓት፤ ለአጀንዳ 2063 ስኬት” በሚል መሪ ሐሳብ ዛሬና ነገ በኅብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ይካሄዳል። ጉባዔው ኢትዮጵያ አኅጉራዊ የፖለቲካ እና ዲፕሎማሲያዊ መድረክ መሆኗን ዳግም የምታሳይበት ነው።
"ጉማታ" በረከትን የመጋራት እሴት!!
Feb 6, 2026 526
"ጉማታ" በረከትን የመጋራት እሴት!! በያንተስራ ወጋየሁ -ዲላ ቀን ቀንን እየወለደ ጊዜ ሳያቋርጥ እንደ ዥረት መፍሰሱን አያቆምም። ትናንት አዲስ የነበረው አሮጌው የሚባልበት፣ ዛሬ አዲስ ሆኖ ነገ አሮጌ ለመባል ይሮጣል። ወቅቶች ይፈራረቃሉ፣ ይመሻል፣ ይነጋል፣ ትናንት ለዛሬ፣ ዛሬ ለነገ እንዲህ እንዲህ እየተቀባበሉ ዘመን ዘመንን እየተካ ዛሬ ላይ ተደርሷል።   በጥምር ግብርናውና በቡናው የሚታወቀው ጌዴኦ ትናንትን ሸኝቶ ዛሬን እንደ አዲስ ለመቀበል ሽር ጉድ እያለ ነው። በክረምቱ የተዘራው ሰብል ተሰብስቦ ወደ ጎተራ እንዳስገባ ጌዴኦ አዲስ ዓመቱን ‹‹ዳራሮ››ን ይቀበላል። ዳራሮ የተጣላ የሚታረቅበት፣ ቂም የያዘ ቂምና ቁርሾውን የሚተውበት፣ ወጣቶች የሚተጫጩበት፣ አዛውንቶች ወደ ሽምግልና የሚሸጋገሩበት እሴቶችን በውስጡ የያዘ ነው።   "ያገኘሁትን ምርት ብቻዬን አልበላም" ብሎ የሚያምነው የጌዴኦ አርሶ አደር ካመረተው ምርት ለመሪው፣ ልጆች ለወላጆችና ለአሳዳጊዎቻቸው፣ አዲስ ተጋቢዎች ለአማቾቻቸው፣ ቂም የያዘ ሰው እንዲሁ የተቀየመውን ሰው ይቅርታ ለመጠየቅ ጉማታ ይዘው ይሄዳሉ። "ጉማታ" በጌዴኦ ዘመን መለወጫ ወቅት የሚፈጸም ስጦታ ነው። ጉማታ በቤት ውስጥ ተዘጋጅቶ ወደ ታላላቆች ቤት ወይም ወደ ማኅበረሰቡ አደባባይ የሚወሰድ በመሆኑ፣ የግለሰብን ደስታ ወደ ማህበረሰባዊ ደስታ የሚቀይር ድልድይ ነው። በአጠቃላይ ጉማታ ከሌለ የዳራሮ በዓል ሙሉ አይሆንም። ጉማታ የጌዴኦን ሕዝብ አንድነት የሚያጸና፣ ትውልድን ከትውልድ የሚያስተሳስር ሀገር በቀል እሴት ነው። በዳራሮ በዓል አከባበር ውስጥ "ጉማታ" እጅግ አስፈላጊና ትልቅ ትርጉም ያለው ባህላዊ የክብር ስጦታ የመስጠት ሥርዓት ነው። "ጉማታ" ማለት በቀጥታ ትርጉሙ "ስጦታ" ማለት ቢሆንም፣ በጌዴኦ ባህል ግን ከስጦታ በላይ ነው። ምስጋናን፣ ፍቅርን፣ አክብሮትንና በረከትን የመጋራት መገለጫ ነው።   የጌዴአ ባህላዊ የባሌ ስርዓት መሪ ሆነው የሚሰየሙት አባ ገዳ ለህዝብ ከመጸለይ፣ ከማስታረቅና ክፉን በማውገዝ ህዝቡ ተፈጥሮን እንዲንከባከብ ከማስተማር ውጭ አይዘሩም፣ አይነግዱም፣ አልፎም እንሳስትን አያረቡም፡፡ የዳራሮ በዓልን ተከትሎ ህዝቡ የሚያቀርብላቸውን "ጉማታ" በመቀበል ባህላዊ የመሪነት ሚናቸውን በአግባቡ ከመወጣት ውጪ። ኑሮው ከጥምር እርሻ ጋር የተቆራኘው የጌዴኦ ሕዝብ ዘርቶ ካጨደው፣ አርብቶ ካገኘው ከብት፣ አንቦ ከቆረጠው ማር፣ ከሁሉም በአይነት በአይነቱ ሸክፎ ዳራሮ ወደ ሚከበርበት ሶንጎ (አደባባይ) ይተማል። ለጉማታ ከሚቀርቡ ከፍተኛ ዋጋ ያላቸው ስጦታዎች አንዱ ማር ነው። ማር በጌዴኦ ዘንድ የጣፋጭ ዘመንና የጤና ምልክት ተደርጎ ይወሰዳልና ዋናው ስጦታ ነው። ጌዶኦዎች ቡና፣ ቅቤና ባህላዊ ምግቦች፣ የቁም እንስሳት በግና ስንጋ እንዲሁም ገንዘብ በመያዝ በበዓሉ ውስጥ የጉማታ ስርዓት ሲደርስ ተሽቀዳድመው ለአባ ገዳው በመስጠት ምርቃት ይቀበላሉ።   "ጉማታ" የተቀበለው ሰው የሚመርቀው ምርቃት በሰጪው ሕይወት ላይ ትልቅ ለውጥ እንደሚያመጣ ይታመናልና ከስጦታው ይልቅ ምርቃቱ ትልቅ ዋጋ አለው። "ያገኘሁትን ምርት ብቻዬን አልበላም" ብሎ የሚያምነው ጌዴኦ በረከትን ማካፈል ለቀጣዩ ዓመት ተጨማሪ በረከት እንደሚያገኝ ስለሚያውቅ ጉማታ መስጠት የዘመናት ቅርሱ ነው። ጉማታ ከአባ ገዳና ከባህል ሽማግሌዎች ባለፈ አርሶ አደሩ ከማጋኖ (ከፈጣሪ) ያገኘውን በረከት ለሚወዳቸውና ለሚያከብራቸው ሰዎች የሚያቀርብበት መንገድ መሆኑን የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ገልጸዋል።   ልጆች ለወላጆቻቸውና ለቤተሰብ አባላት ላሳደጓቸውና ለሰጧቸው ምርቃት ምስጋናቸውን ለመግለጽ ጉማታ ይዘው ይሄዳሉ። በቅርቡ ጋብቻ የመሠረቱ ወጣቶች ወደ አማቾቻቸው ቤት ጉማታ ይዞ በመሄድ ዝምድናቸውን ያጠናክራሉ። በዓመቱ ውስጥ ቅሬታ ወይም ቂም ካለ፣ በዳራሮ ወቅት ጉማታ ይዞ በመሄድ ይቅርታ ይጠየቃል። ጉማታ የሰውን ልብ ለማለስለስና አዲስ ዓመትን በሰላም ለመጀመር ያገለግላል ተብሎ ስለሚታመን። ጉማታ በቤት ውስጥ ተዘጋጅቶ ወደ ታላላቆች ቤት ወይም ወደ ማህበረሰቡ አደባባይ የሚወሰድ በመሆኑ፣ የግለሰብን ደስታ ወደ ማህበረሰባዊ ደስታ የሚቀይር ድልድይ ስለመሆኑም ነው ዋና አስተዳዳሪው የጠቆሙት። በአጠቃላይ ጉማታ ከሌለ የዳራሮ በዓል ሙሉ አይሆንም። ጉማታ የጌዴኦን ሕዝብ አንድነት የሚያጸና፣ ትውልድን ከትውልድ የሚያስተሳስር ሀገር በቀል እሴት ነው። ይህም የመደጋገፍ እሴትን ከማጠናከር በተጓዳኝ ህዝቡ የመንግስት ገቢን እንዲሁም በማህበረሰብ ተሳትፎ ለሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ግንባር ቀደም ተሳታፊ እንዲሆን መሰረት የጣለ ነው ይላሉ።   የዘንድሮው ዳራሮ ከቤት በተለይም ከአባ ገዳው መኖሪያ አንስቶ በሶንጎዎችና በየደረጃው በሚገኙ መዋቅሮች በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት ጭምር እየተከበረ መሆኑን ያነሱት አስተዳዳሪው ጉማታም ዋናው የበዓሉ እሴት ሆኖ እየተከበረ ነው ብለዋል። ባህልና ማንነትን በማስጠበቅና በማዳበር፣ ባህሉ ወደ ወጣቶች እንዲተላለፍ በማበረታታት እንዲሁም የጌዴኦ ባህልን ለሌሎች ህዝቦች ለማስተዋወቅና የማህበረሰብ አንድነትና ባህላዊ እሴትን ለማጠናከር እያገለገለ ያለው የጌዴኦ ዘመን መለወጫ ዳራሮ ጥር 29 እና 30 በዲላ ከተማ ይከበራል። የዳራሮ በዓል የጌዴኦን ሕዝብ የሥራ ባህል፣ የተፈጥሮ ጥበቃ ዕውቀትና የሰላም እሴት ለዓለም የሚያሳይ ትልቅ አጋጣሚ ነው። ይህ በዓል በተለይ የጌዴኦ የባህላዊ መልክዓ ምድር (Cultural Landscape) በዩኔስኮ (UNESCO) በዓለም ቅርስነት መመዝገቡን ተከትሎ፣ አሁን ላይ ከቤትና ከአደባባይ አልፎ ዓለም አቀፋዊ ትኩረት እያገኘ ያለ ታላቅ እሴት ሆኗል። የዓመት ሰው ይበለን!!
ዕድሜ  ያልገደበው የልማት አርበኝነት 
Jan 14, 2026 709
ዕድሜ ያልገደበው የልማት አርበኝነት ብርቱዎች ነገን በማሰብ ሁሌም ታትረው ይሰራሉ፤ ይደክማሉ፤ ይጥራሉ…ለቀጣዩ ትውልድም ጥሪት በማስቀመጥ አሻራቸውን ያኖራሉ። አገር የምትገነባው በትውልድ ቅብብሎሽ ነው። “አባት ያበጀው፤ ለልጅ ይበጀው” እንደሚባለው ልጆች ከአባቶቻቸው ያገኙትን ጥሪት በአዲስ እውቀትና አሰራር ለአገር እድገት በሚበጅ መልኩ አጠናክረው መጠቀማቸው አይቀርም። “ዕድሜ ጸጋ ነው” የሚለው አባባል አንዳንዴ በዕድሜ ብንገፋም ጠንክረን ከሰራን ብዙ ነገር እናያለን ከሚለው ጋር የተያያዘ ነው። በሰቆጣ ከተማም እድሜ ሳይገድባቸው በልማት ውጤታማ የሆኑ ግለሰቦች ለዚህ ማሳያ ናቸው። የከተማዋ ነዋሪ የ67 ዓመቱ አቶ ብርሃኑ አወቀ እና የ83 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ አቶ ታደሰ አዳነ ዕድሜያቸው ቢገፋም ጠንክሮ ከተሰራ ውጤታማ መሆን እንደሚቻልና ዕድሜ ጸጋ ሆኖ ብዙ ለውጥ ማየት እንደሚቻል ማሳያ ናቸው። ግለሰቦቹ ከዕድሜ ብዛት ጉልበቴ ደከመ፣ አይኔ ፈዘዘ፣ እጄም ተሳሰረ…ሳይሉ ጊዜያቸውን በደን፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሥራ በማሳለፍ ለወጣቶች የልማት አርአያነት ያለው ተግባር እየፈጸሙ ነው። አቶ ብርሃኑ አወቀ በሰቆጣ ከተማ ዳርቻ የሚገኝ አለቱ ያገጠጠና የተራቆተ አካባቢን ከሌላ አካባቢ ለም አፈር በማምጣትና በመደልደል አትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም ደን በማልማት ውጤታማ ስራ እያከናወኑ ነው።   ከመንግስት ሥራ በጡረታ ከወጣሁ ጀምሮ ጠንክሬ በመስራት የምለወጥበትን ሥራ ማሰብ ስነበረብኝ፤ የቆሻሻ መጣያ ሆኖ ለዘመናት የቆየን ጭንጫ መሬት ጠርጌና ደልድዬ ማልማት ችያለሁ ይላሉ ወደኋላ መልስ ብለው የተነሱበትን ሁኔታ ሲያስታውሱ። ግማሽ ሄክታር በማይሞላ መሬት ላይ ፓፓያ፣ ሙዝ፣ ዘይቱና፣ ጌሾ፣ ቡና፣ ማንጎና አቮካዶ አልምተዋል። በተጨማሪም ቆስጣ፣ ቲማቲም፣ ጥቅል ጎመንና ሽንኩርት በማምረት ከቤት ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ጥሪት አፍርተዋል።   ጊዜን በአግባቡ ተጠቅሞ ተግቶ መስራት ከተቻለ ሀብት ማፍራትና ህይወትንም መለወጥ እንደሚቻል የገለጹት አቶ ብርሀኑ፣ ወጣቱም ከእሳቸው የሥራ ትጋት በመማር በአካባቢው ያለውን ፀጋ ለይቶ በማልማት ሊጠቀም ይገባል ሲሉ ይመክራሉ። ሌላው የ83 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ አቶ ታደሰ አዳነ ባለፉት 18 ዓመታት በተሰማሩበት የአትክልትና ደን ልማት ሥራ የአካባቢያቸውን ገጽታ ቀይረዋል። የዕድሜ ዘመናቸውን በውትድርናና በመንግስት ሠራተኝነት በማገልገል ሃገራዊ ግዳጃቸውን ሲወጡ ነው የቆዩት።   ከመንግስት ሥራ በጡረታ ከተገለሉ በኋላም ቤት ውስጥ መቀመጥን አልመረጡት። አካፋና ዶማቸውን ይዘው ባላቸው ትንሽ መሬት ላይ ጌሾ፣ ዘይቱና እና ማንጎ በማልማት ምርቱን ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ሆነዋል። በአካባቢያችን ያሉ ፀጋዎችን በአግባቡ ለይተን ማልማት ከቻልን ድህነትን ማስወገድ የሚከብድ አይሆንም ያሉት አቶ ታደሰ፣ የተራቆተና በጎርፍ የተጎዳን መሬት በማልማት አካባቢውን ሳቢና ማራኪ ማድረጋቸውን ነው የገለጹት። ወጣቱም ከእሳቸው አርአያነት ያለው ተግባር በመማር በአካባቢው እጁ ላይ ባለ ሀብት ሰርቶ መለወጥ እንደሚቻል በተግባር ማሳየት እንዳለበት መክረዋል።   የዋግኸምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ግብርና መምሪያ የአትክልትና ፍራፍሬ መስኖ ውሃ አጠቃቀም ቡድን መሪ አቶ ደሳለኝ አዳነ እንደገለጹት፤ በብሔረሰብ አስተዳደሩ 24ሺህ 847 አርሶ አደሮች በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተዋል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል ዕድሜ ሳይገድባቸው ወደ ልማት የገቡ አረጋዊያን እያከናወኑት ያለው የግብርና ልማት ሥራ ለወጣቱ ትልቅ ትምህርት እንደሚሆንም ተናግረዋል። ከእነሱ ልምድ በመውሰድ በዞኑ ወጣቶች፣ ሴቶችና አረጋዊያን በጓሮና ባላቸው መሬት ላይ አትክልትና ፍራፍሬ እንዲያለሙ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸው ይህም በዞኑ የሚስተዋለውን የስርዓተ ምግብ ችግር ለማሻሻል ያግዛል ብለዋል።
ከማላጋ እስከ አፍሪካ ዋንጫ፤ የሞሮኮው አዲስ እንቁ ብራሂም ዲያዝ
Jan 13, 2026 649
  የግል ክህሎት፣ ፈጣን አስተሳሰቡ እና በጠባብ ክፍተቶች ውስጥ ሰብሮ የመግባት አቅሙ ሙገሳ እንዲጎርፍለት አድርጓል። አንድ ለአንድ ሲገናኝ ተከላካዮችን በፈጣን አካላዊ ቅልጥፍና እና በድንገት አቅጣጫ በመቀየር የሚያልፍበት መንገድ እንዲሁም የመፍጠር አቅሙ የተመልካቾችን ቀልብ የሚይዝ ነው። የአማካይ እና የአጥቂ መስመርን በማገናኘት እና በአስገራሚ ሁኔታ አጭር ኳሶችን በማቀበልም የተዋጣለት ተጫዋች ነው ማለት ይቻላል። በቦታ አያያዙ የእግር ኳስ ልኅቀቱ ከፍተኛ ነው የሚል አድናቆት ከእግር ኳስ ባለሙያዎች አግኝቷል። ኳስን ሲያንከባልልም ለዐይን ይስባል። ከክህሎቱ እና ከማራኪ እንቅስቃሴው ባለፈ ወደ ኋላ እየመለሰ ተከላካዮችን ያግዛል፣ ኳስ ይነጥቃል። ይህ ተጫዋች የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ክስተት የሆነው የሞሮኮው ብራሂም ዲያዝ ነው። የ26 ዓመቱ የሪያል ማድሪድ የክንፍ መስመር ተጫዋች ዲያዝ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ አምስት ጨዋታዎችን አድርጎ አምስት ግቦችን በማስቆጠር የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። አዘጋጇ ሞሮኮ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ መክፈቻ ኮሞሮስን 2 ለ 0 ስታሸንፍ የውድድሩን የመጀመሪያ ግብ አስቆጥሯል።   ብራሂም አብዱልቃድር ዲያዝ የተወለደው እ.አ.አ ኦገስት 3 ቀን 1999 በስፔን ማላጋ ግዛት ነው። እናቱ ስፔናዊ አባቱ ሞሮኳዊ ናቸው። ዲያዝ ያደገው በማላጋ ነው። እግር ኳስንም በአንዳሉሺያዊቷ ከተማ ሲጫወት ቆይቷል። በ16 ዓመቱ ካደገበት ማላጋ በመውጣት እ.አ.አ በ2015 ወደ ማንችስተር ሲቲ ወጣት አካዳሚ በ200 ሺህ ፓውንድ ወጪ ተዘዋወረ። ዲያዝ እ.አ.አ ሴፕቴምበር 21 ቀን 2016 በካራባኦ ካፕ (በቀድሞ አጠራሩ ሊግ ካፕ) ማንችስተር ሲቲ ከስዋንሲ ሲቲ ባደረገው ጨዋታ በ80ኛው ደቂቃ በኬሌቺ ኢናቺዩ ተቀይሮ በመግባት ለውኃ ሰማያዊዎቹ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የመጀመሪያውን ጨዋታ ካደረገ ከሶስት ቀናት በኋላ ከማንችስተር ሲቲ ጋር ለሶስት ዓመታት የሚያቆየውን ፕሮፌሽናል ኮንትራት ተፈራርሟል። እ.አ.አ ኖቬምበር 21 ቀን 2017 ማንችስተር ሲቲ ከፌይኖርድ ሮተርዳም ጋር ባደረገው የሻምፒዮናስ ሊግ ጨዋታ ላይ የመጀመሪያ የአውሮፓ መድረክ ጨዋታውን ማድረግ ችሏል። በወቅቱ ብራሂም ስተርሊን መደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በጭማሪ ሰዓት ላይ ነበር ተቀይሮ የገባው። ዲያዝ በውኃ ሰማያዊዎቹ ማልያ ቋሚ አሰላለፍ ውስጥ ገብቶ የተጫወተው እ.አ.አ ዲሴምበር 19 ቀን 2017 ነው። ማንችስተር ሲቲ ከሌስተር ሲቲ በካራባኦ ካፕ ጨዋታ ላይ ለ88 ደቂቃዎች ተሰልፎ ተጫውቷል።   እ.አ.አ ጃንዋሪ 20 ቀን 2018 ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 3 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። በወቅቱ ማንችስተር ሲቲ የሊጉን ዋንጫ ያነሳ ሲሆን፤ በውድድር ዓመቱ አራት ጨዋታዎች ላይ ብቻ ተሳትፎ ያደረገው ብራሂም ዲይዝ የሜዳሊያ ሽልማት አግኝቷል። እ.አ.አ ኦገስት 5 ቀን 2018 ማንችስተር ሲቲ ቼልሲን 2 ለ 0 ባሸነፈበት የኮሙዩኒቲ ሺልድ ጨዋታ ላይ በፊል ፎደን ተቀይሮ በመግባት ለ15 ደቂቃዎች ተጫውቷል። ዲያዝ እ.አ.አ 2018/19 ማብቂያ ላይ ማንችስተር ሲቲ ፉልሃምን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የመጀመሪያ ግቦቹን ለሲቲ አስቆጥሯል። በማንችስተር ሲቲ ያለው ውል እ.አ.አ 2019 ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ወቅት ስሙ ከዝውውር ጋር በስፋት ይነሳ ነበር። ዲያዝ እ.አ.አ ጥር 2019 በ17 ሚሊዮን ዩሮ ከማንችስተር ሲቲ ወደ ሪያል ማድሪድ ተዘዋወረ። ለስድስት ዓመታት የሚያቆየውን ውልም ፈርሟል። የክንፍ ተጫዋቹ የመጀመሪያ ጨዋታውን በነጮቹ ማልያ ያደረገው እ.አ.አ ጥር 9 ቀን 2019 ሪያል ማድሪድ ሌጋኔን በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ 3 ለ 0 ባሸነፈበት ወቅት ነው። ከአራት ቀናት በኋላ በስፔን ላሊጋ ሪያል ማድሪድ ሪያል ቤቲስን 2 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ ተቀይሮ በመግባት በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የመጀመሪያ ግቡን ለማስቆጠር ሶስት ወራትን ጠብቋል። እ.አ.አ ግንቦት 12 ቀን 2019 ሪያል ማድሪድ በላሊጋው በሪያል ሶሲዬዳድ 3 ለ 1 ሲሸነፍ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በወቅቱ ዲያዝ ስድስት ጨዋታዎች ላይ በላሊጋው የተጫወተ ሲሆን፤ በመጀመሪያ ዓመቱ የሊጉን ዋንጫ አንስቷል። ሪያል ማድሪድ እ.አ.አ በ2021/21 የውድድር ዓመት ብራሂም ዲያዝ ወደ ኤሲ ሚላን በውሰት ማምራቱን ይፋ አደረገ። ዲያዝ ሚላን እ.አ.አ መስከረም 27 ቀን 2020 ክሮቶኔን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ የመጀመሪያ ግቡን ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ ግንቦት 2021 ኤሲ ሚላን ጁቬንቱስን 3 ለ 0 ሲያሸንፍ ያስቆጠረው ግብም ተጠቃሽ ነው። ዲያዝ በኤሲ ሚላን የውሰት ውሉ ሲያበቃ በድጋሚ ለሁለት ዓመታት በውሰት የሚቆይበት ስምምነት ሪያል ማድሪድ ከጣልያኑ ክለብ ጋር የተፈራረመ ሲሆን፤ ውሉ ሚላን ተጫዋቹን የማቆየት መብት ሰጥቶታል። እ.አ.አ መስከረም 15 ቀን 2021 ኤሲ ሚላን በሻምፒዮንስ ሊጉ የ3 ለ 2 ሽንፈት ሲያስተናግድ የመጀመሪያ የአውሮፓ መድረክ ግቡን አስቆጥሯል። በ2023 ኤሲ ሚላን ቶተንሃም ሆትስፐርስን በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ጥሎ ማለፍ 1 ለ 0 ሲያሽንፍ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ በ2023 ሰኔ ወር ላይ ሪያል ማድሪድ ዲያዝ ከኤሲ ሚላን የሶስት ዓመታት የውሰት ቆይታ በኋላ ወደ ክለቡ መመለሱን አሳውቋል። ተጫዋቹ በኤሲ ሚላን ቆይታው 91 ጨዋታዎችን አድርጎ 13 ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ዲያዝ ወደ ሪያል ማድሪድ ከተመለሰ በኋላ ኮንትራቱን እስከ 2027 አራዝሟል። እ.አ.አ መስከረም 27 ቀን 2023 ወደ ክለቡ ከተመለሰ በኋላ ሪያል ማድሪድ ላስ ፓልማስን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ ግብ አስቆጥሯል።   የክንፍ መስመር ተጫዋቹ ሪያል ማድሪድ በሀገር ውስጥ እና በአውሮፓ መድረክ በሚያደርጋቸው ጨዋታዎች ላይ ግብ በማስቆጠር እና ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል። ዲያዝ እስከ አሁን ለሪያል ማድሪድ ባደረጋቸው 129 ጨዋታዎች 20 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከነዚህም ውስጥ 13ቱ በላሊጋው ያስቆጠራቸው ናቸው። ከክለብ ወጣ ስንል የተጫዋቹን የብሔራዊ ቡድን ቆይታ እናገኛለን። ዲያዝ በታዳጊነቱ በተለያዩ የእድሜ እርከኖች ለስፔን ወጣት ቡድኖች ተጫውቷል። እ.አ.አ በ2016/17 የውድድር ዘመን ለስፔን ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በ16 ዓመቱ ተሰልፎ መጫወት ችሏል። በተለይም አዘርባጃን እ.አ.አ በ2017 ባዘጋጀችው 15ኛው የአውሮፓ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ላይ ያሳየው ድንቅ ብቃት አድናቆት አስችሮታል። በዚያ ቀጥለው በነበሩ ዓመታትም ለስፔን ከ19 እና ከ21 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድኖች ተጫውቷል። ብራሂም ዲያዝ በስፔን ታዳጊና ወጣት ቡድኖች ላይ በአጠቃላይ 28 ጨዋታዎችን አድርጎ ስድስት ግቦችን አስቆጥሯል። የስፔን ታዋቂ የስፖርት ጋዜጣ ማርካ እ.አ.አ ጥር 23 ቀን 2023 ለሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን መጫወት ማቀዱን የሚመለከት ዘገባ ይዞ ወጥቷል። ከዜግነቱ ጋር በተያያዘ ያሉ አንዳንድ የአስተደዳር ጉዳዮች በወቅቱ መፍትሄ አግኝተዋል። ይሁንና ኮትዲቯር እ.አ.አ በ2023 ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሞሮኮው አሰልጣኝ ዋሊድ ሬግራጉዊ ከተጫዋቹ ጋር በተደረገ የቅድሚያ ስምምነት ለተጫዋቹ ጥሪ አልተደረገለትም። ዲያዝ እ.አ.አ መጋቢት 10 ቀን 2024 ለሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለሀገሪቷ ብሔራዊ መጫወት እንደሚፈልግ በይፋ ማሳወቁን ማርካ በወቅቱ ዘግቧል። ጥያቄውም ተቀባይነት አገኘ። በወቅቱ የሞሮኮ አሰልጣኝ ዋሊድ ሬግራጉዊ ብሔራዊ ቡድኑ ከአንጎላ እና ሞሪታኒያ ጋር ለነበረበት የወዳጅነት ጨዋታ ለዲያዝ ጥሪ አድርገውለታል። እ.አ.አ መጋቢት 22 ቀን 2024 ሞሮኮ አንጎላን 1 ለ 0 ባሸነፈችበት ጨዋታ ለብሔራዊ ቡድኑ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። እ.አ.አ ጥቅምት 6 ቀን 2024 ሞሮኮ ለ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከጋቦን ጋር ባደረገችው ጨዋታ 4 ለ 1 ስታሸንፍ የመጀመሪያ ግቡን ለሞሮኮ ማስቆጠር ቻለ። እ.አ.አ ሕዳር 15 ቀን 2024 ሞሮኮ በማጣሪያው ጋቦንን 5 ለ 1 ስትረታ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ማሳረፍ ችሏል። ከሶስት ቀናት በኋላ ሞሮኮ ከሌሴቶ ጋር ባደረገችው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታ 7 ለ 0 ስታሸንፍ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር በሀገሩ ማልያ የመጀመሪያ ሀትሪኩን ሰርቷል። እ.አ.አ ጥቅምት 2025 ሞሮኮ ራባት ላይ ኮንጎ ሪፐብሊክን 1 ለ 0 በማሸነፍ በስፔን ከዚህ ቀደም በብሔራዊ ቡድን ደረጃ ተይዞ የነበረውን 15 ተከታታይ ጨዋታዎችን የማሸነፍ ክብረ ወሰን በመስበር ወደ 16 ማድረስ ችላለች። በዚህ ታሪካዊ ጨዋታ ላይ ዲያዝ ተሰልፎ ተጫውቷል። የሞሮኮ ተከታታይ የማሸነፍ ጉዞ 19 ጨዋታዎች ደርሶ የነበረ ሲሆን በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከማሊ ጋር አንድ አቻ ስትለያይ አብቅቷል።   ሞሮኮ ለ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በማጣሪያ ብታልፍም አስቀድማ ውድድሩን እንድታዘጋጅ እድል አግኝታ የነበረው ጊኒ በዝግጅት ማነስ ምክንያት በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ከሁለት ዓመት በፊት አዘጋጅነቷ ተነጥቆ ለሞሮኮ ተሰጥቷል። ሞሮኮ የዘንድሮውን ውድድር በደማቅ ሁኔታ እያካሄደች ትገኛለች። በውድድሩ ላይ ጎልተው ከታዩ ተጫዋቾች መካከል ብራሂም ዲያዝ ተጠቃሽ ነው። በአፍሪካ ዋንጫው እስከ አሁን ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። በተሰለፈባቸው በእያንዳዱ ጨዋታዎች ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ለሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን በአምስት የአፍሪካ ዋንጫ ተከታታይ ጨዋታዎች ግብ ያስቆጠረ የመጀመሪያው ተጫዋች በመሆን አዲስ ታሪክ ጽፏል። ሞሮኮ በሩብ ፍጻሜው ማሊን 2 ለ 0 ስታሸንፍ የመጀመሪያውን ጎል አስቆጥሯል። ሀገሩ ወደ ግማሽ ፍጻሜ እንድታልፍ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱንም እየመራ ይገኛል። ሞሮኮ በዚሁ ግስጋሴዋ ከቀጠለች ዲያዝ የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ እና ኮከብ ተጫዋች የመሆን እድሉ ሰፊ ነው። ሞሮኮ በግማሽ ፍጻሜው ከናይጄሪያ ጋር ረቡዕ ጥር 6 ቀን 2018 ዓ.ም በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ታደርጋለች። ዲያዝ በዚህ ጨዋታ ላይ ልዩነት ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል። አንዳንድ የእግር ኳስ ተንታኞች ብራሂም ዲያዝ እ.አ.አ በ2026 ወጥነት ያለው ብቃት ማሳየት ከቻለ የአፍሪካ ኮከብ ተጫዋችነት ሽልማቱን የሚወስድበት የለም እያሉ ይገኛሉ። ሞሮኳውያን በተጫዋቹ ፍቅር ልባቸው ከንፏል። በየጨዋታው ዲያዝ ዲያዝ እያሉ ከፍተኛ ድጋፍ እና ሙገሳ እየሰጡት ይገኛሉ። እሱም በድንቅ ብቃቱ ምላሽ እየሰጣቸው ነው። በተወለደበት ማላጋ ከተማ የጀመረው የእግር ኳስ ሕይወት በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የበለጠ አብቧል። የሞሮኮው አዲሱ ኮከብ ብራሂም ዲያዝ ቀጣይ የእግር ኳስ ሕይወት በስኬት እና በድል የደመቀ እንደሚሆን ከአሁኑ ድንቅ ብቃቱ ተነስቶ መናገር ይቻላል።
አማድ ዲያሎ - የአፍሪካ እግር ኳስ  ብሩህ ተስፋ
Jan 9, 2026 850
ተጫዋቹ አዲሱ ሳሙኤል ኤቶ የሚል ስያሜ እየተሰጠው ይገኛል። ፍጥነቱን ከዲዲየር ድሮግባ ጋር ያነጻጽሩታል። ለተጋጣሚ ተጫዋቾች የራስ ምታት እና ፈተና የሆነውን ግራ እግሩን ከሌላኛው የግራ እግር ምትሃተኛ ሪያድ ማህሬዝ ጋር የሚያወዳድሩም አልጠፉም።   በዚህ አካሄዱ ከቀጠለ ያለ ምንም ጥርጥር ወደፊት በእግር ኳስ ከምንመለከታቸው ኮከቦች አንዱ ሊሆን ይችላል እየተባለለት ይገኛል። ይህ ተጫዋች በማንችስተር ዩናይትድ የ147 ዓመታት ታሪክ ሀትሪክ የሰራ የመጀመሪያው አፍሪካዊ ተጫዋች ነው። እያወራን የምንገኘው የማንችስተር ዩናይትድ 16 ቁጥር ማልያ ለባሽ አማድ ዲያሎ ነው። የ23 ዓመቱ ኮትዲቯራዊ ተስፈኛ ተጫዋች በቀያዮቹ ሴጣኖች እያሳየ ያለው ብቃት ከብዙዎች ዘንድ ሙገሳ አስችሮታል፣ አድናቆት እንዲጎርፍለት አድርጓል። ወደ ኋላ መለስ እንበልና የአማድ ዲያሎን መነሻ እንመልከት። ካሜሮን ከአዘጋጇ ሞሮኮ ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው አማድ የተወለደው እ.አ.አ ጁላይ 11 2002 በኮትዲቭዋር መዲና አቢጃን ነው። ተጫዋቹ በአፍሪካ ምድር ቢወለድም ገና በህጻንነት እድሜው ነበር ወደ ጣልያን የተሰደደው። የእግር ኳስ ህይወቱን የጀመረው እ.አ.አ በ2014 በጣልያን ሬጂዮ ኢሚሊያ ግዛት በሚገኘው ቦካ ባርኮ የታዳጊ ቡድን ነው። ቡድኑን በተቀላቀለበት ዓመት የገና በዓል (ክሪስማስን) በማስመልከት በተካሄደ ውድድር ላይ በ12 ዓመቱ ኮከብ ግብ አግቢ ሲሆን ያሳየው አስደማሚ ብቃት የብዙዎችን ቀልብ ሳበ። ይህ የገና በዓል ውድድር አማድን እ.አ.አ በ2015 በቦካ ባርኮ ቡድን እንዲመዘገብ አደረገው። ተጫዋቹ በቡድኑ ብዙም አልቆየም። የበርካታ የጣልያን ሴሪአ ክለቦች አይን አረፈበት። ብዙም ሳይቆይ በዛው በ2015 ወደ ጣልያኑ አትላንታ አመራ።   አማድ ከእ.አ.አ 2015 እስከ 2019 ለአትላንታ ታዳጊ ቡድን የተጫወተ ሲሆን እ.አ.አ 2019 እና 20 ለዋናው ቡድን ተጫውቷል። ለዋናው ቡድን አራት ጨዋታዎችን አድርጎ ማስቆጠር የቻለው አንድ ግብ ብቻ ነው። የእንግሊዙ ክለብ ማንችስተር ዩናይትድ ተጫዋቹ በጣልያኑ ክለብ ባሳየው ብቃት በ18 ዓመት እድሜው እ.አ.አ ጃንዋሪ ወር 2021 በአምስት ዓመት ኮንትራት በ37 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዩሮ አስፈርሞታል። ተጫዋቹ ወደ ማንችተር ሲመጣ ቀጥታ ወደ ዋናው ቡድኑ አልተቀላቀለም። በቡድኑ ከ23 ዓመት በታች ጨዋታውን ማድረግ ጀመረ። አማድ የመጀመሪያ ጨዋታውን ለማንችስተር ያደረገው እ.አ.አ ፌብሩዋሪ 18 2021 ቡድኑ ከሪያል ሶሲዬዳድ ጋር ባደረገው የዩሮፓ ሊግ ጨዋታ ነው። በዛው ዓመት በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ እና አውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ዲያሎ ከእ.አ.አ 2022-2023 ባለው ጊዜ ሬንጀርስ እና ሰንደርላንድ በውሰት የተጫወተ ሲሆን በቡድኖቹ ባደረጋቸው 47 ጨዋታዎች 16 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል።   እ.አ.አ በ2023/24 አማድ ወደ ማንችስተር ዩናይትድ በመመለስ በድጋሚ መጫወት ጀምሯል። በክለቡም ድንቅ ብቃቱን እያሳየ መምጣት ጀመረ። እ.አ.አ ጥር 17 2025 ማንችስተር ዩናይትድ ከሊጉ ከወረደው ሳውዝሃምፐን ጋር በነበረው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መርሃ ግብር በ12 ደቂቃ ውስጥ ሶስት ግቦችን አስቆጥሮ ሀትሪክ በመስራት ቡድኑ 3 ለ 1 አንዲያሸንፍ ያደረገበት መንገድ አድናቆት አስችሮታል። በዚህም አማድ በማንችስተር ዩናይትድ የ147 ታሪክ የመጀመሪያ ሀትሪክ የሰራ አፍሪካ ተጫዋች በመሆን አዲስ ታሪክ ጽፏል። አማድ በቀያዮቹ ሴጣኖች ማልያ እስከ አሁን ባደረጋቸው 53 ጨዋታዎች 11 ግቦችን አስቆጥሯል። ተጫዋቹ ከክለቡ በተጨማሪ ለኮትዲቯር ብሄራዊ ቡድን በመጫወት ላይ ይገኛል። እ.አ.አ 2021 ኮትዲቯር ከኒጀር ጋር ባደረገችው ጨዋታ በ86ኛው ደቂቃ ተቀይሮ በመግባት ለብሄራዊ ቡድኑ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ለሀገሩ እስከ አሁን ባደረጋቸው 15 ጨዋታዎች አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። የመጀመሪያ ጎሉን ኮትዲቯር በ2021 በወዳጅነት ጨዋታ ቡርኪናፋሶን 2 ለ 1 ስታሸነፍ ነበር ያስቆጠረው። አማድ ዲያሎ ዘንድሮ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ድንቅ ጊዜ እያሳለፈ ይገኛል። አማድ በውድድሩ ላይ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሶስት ግቦችን ያስቆጠረ ሲሆን አንድ ለግብ የሚሆን ግብ አመቻችቶ አቀብሏል። ኮትዲቯር ከሞዛምቢክ፣ ካሜሮን እና ቡርኪናፋሶ ጋር ባደረገቻቸው ጨዋታዎች የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተምርጧል። የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ሩብ ፍጻሜ እንድትደርስ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል። ኮትዲቯር ከግብጽ በሩብ ፍጻሜው ነገ ከግብጽ ጋር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በአጋዲር ስታዲየም የምታደርገው ጨዋታ በጉጉጉት ይጠበቃል። ሀገሩ በጠዋታው ላይ ከአማድ ብዙ ትጠብቃለች። ወደ ክለብ እንቅስቃሴው ስንመለስ አማድ በማንችስተር ዩናይትድ ስብስብ ውስጥ ቁልፍ የሚባል ተጫዋች ነው። ፈጣን ኳስን የማንከበላል ክህሎቱ፣ ፍጥነቱ ፣ የቴክኒክ አቅሙ፣ ጨዋታን የማንበብ ብቃቱ እና ሁለቱንም እግሩን የመጠቀም አቅሙ አልፎም ተጫዋቾችን በቄንጥ የሚያልፍበት መንገድ ተጫዋቹን እያስወደሰው ነው። አማድ ዲያሎ ከክንፍ ተጫዋችነቱ ባሻገር የአጥቂ አማካይ ሆኖ መጫወትም ይችላል። እ.አ.አ በ2020 የ18 ዓመት ልደቱን ተከትሎ ተጫዋቹ ስሙን ከአማድ ትራኦሬ ወደ አማድ ዲያሎ አስቀይሯል። አማድ ካለው ድንቅ ብቃት አንጻር ወደፊት በክለብ እና ብሄራዊ ቡድን ደረጃ ድንቅ ጊዜን ካሳለፉ ታዋቂ የአፍሪካ ተጫዋቾች ተርታ የመሰለፉ ጉዳይ አያጠራጥርም።
በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ብዙ ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን ያቀበሉ ተጫዋቾች
Jan 5, 2026 784
በእግር ኳስ ጨዋታ ከግብ አስቆጣሪዎች ጀርባ ኳስን ፍትፍት አርገው ጨርሰው የሚያቀብሉ ተጫዋቾች አሉ። አንድ ተጫዋች ግብ ሲያገባ ከማግባቱ ባልተናነሰ ማን ኳሱን አቀበለው? የሚለው ጥያቄ በተመልካቾች ይነሳል። በእግር ኳስ እድገት ውስጥ በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ለጎል ኳስ አመቻችተው የሚያቀብሉ ተጫዋቾች ትልቅ ዋጋ ይሰጣቸዋል። ማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን አሰናበተ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች እየተካሄዱ ይገኛሉ።   የ33 ዓመቱ የሴኔጋል አምበል ሳዲዮ ማኔ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ካስቆጠረው አንድ ግብ በተጨማሪ ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል የቀዳሚነቱን ስፍራ ይዟል። ማኔ ሴኔጋል ለሩብ ፍጻሜ እንድታልፍ ያበረከተው አስተዋጽኦ ትልቅ የሚባል ነው። ስምንት ተጫዋቾች በተመሳሳይ ሁለት ለግብ የሚሆኑ ግቦችን አመቻችተው አቀብለዋል።   ናይጄሪያውያኑ አዴሞላ ሉክማን እና አሌክስ ኢዎቢ፣ የሞሮኮው አዝዲን ኡናሂ፣ የአልጄሪያው አኒስ ሃጂ-ሙሳ፣ የቡርኪናፋሶው ዳንጎ ኡታራ፣ የቱኒዚያው ሃኒባል ሜጅብሪ፣ የደቡብ አፍሪካው ላይል ፎስተር እና የታንዛንያ ኖቫቱስ ሞሮሺ በሁለት ግቦች ላይ እጃቸው ያለበት ተጫዋቾች ናቸው።   የናይጄሪያው የክንፍ የመስመር ተጫዋች አዴሞላ ሉክማን ሁለት ግቦችን በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ አስቆጥሯል።   የኮትዲቯሩ ክርስቶፈር ኦፔሪ እና የናይጄሪያው ሳሙኤል ቹኩዌዜ በተመሳሳይ አንድ አንድ ግቦች ከመረብ ላይ እንዲቆጠሩ የቀጥታ ተሳትፎ አድርገዋል።   የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬን (ካፍ) የዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ኮከብ ተጫዋች ምርጫ ላይ ካስቀመጣቸው መመዘኛ መስፈርቶች አንዱ ማን ብዙ ለጎል የሚሆን አቀበለ? የሚለው ይገኝበታል። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እስከ ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን የግብ አግቢዎችና የኳስ አቀባዮቹ ፉክክር በያዘው ግለት ይቀጥላል ተብሎ ይጠበቃል።
ወንድማማቾች በአፍሪካ ዋንጫ 
Dec 29, 2025 701
የአፍሪካ ዋንጫ መልከ ብዙ ውድድር ነው። የሀገራት ተቀናቃኝነት፣ ታሪካዊ ገድሎች፣ አይረሴ የተጫዋቾች የግል ብቃት፣ ጨዋታ ወሳኝ ግቦች እና ዋንጫን ከፍ አድርጎ የማንሳት የኩራት እና የሀገር ፍቅር ስሜት መገለጫዎቹ ናቸው። ከሚቆጠሩ ግቦች እና ዋንጫዎች ባለፈ ቤተሰባዊ ገጽታ ያለው ነው። የአፍሪካ ዋንጫ በርካታ ወንድማማች ተጫዋቾች በአንድ ሀገር ማልያ ሲጫወቱ የተመለከትንባቸው አጋጣሚዎች በርካታ ናቸው። በአህጉራዊው መድረክ የ68 ዓመታት ጉዞ አብረው የተጫወቱ ወንድማቾች በዚሁ ጽሁፍ እንመለከታለን። 1. ኢታሎ እና ሉቺያኖ ቫሳሎ (ኢትዮጵያ)   ኢታሎ ቫሳሎ እና ሉቺያኖ ቫሳሎ በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጫወቱ ወንድማማቾች መሆናቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1962 ባዘጋጀችው ሶስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ የቫሳሎ ወንድማማቾች አንድ ላይ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጫውተዋል። ሉቺያኖ በውድድሩ ላይ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ከግብጹ ባደዊ አብድል ፈታህ ጋር በጋራ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኖ አጠናቋል። ሉቺያኖ የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች ተብሎ የተመረጠ ሲሆን ይህም በውድድሩ ታሪክ የኮከብ ተጫዋችነትን ሽልማት ያገኘ የመጀመሪያው ተጫዋች እንዲሆን አስችሎታል። ኢትዮጵያ በወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫን ማንሳቷ የሚታወስ ነው። 2. ሆሳም እና ኢብራሂም ሀሰን (ግብጽ)   ሆሳም ሀሰን እና ኢብራሂም ሀሰን በአፍሪካ ዋንጫው ስኬታማ የሚባሉ ወንድማማች ተጫዋቾች ናቸው። እ.አ.አ በ1986 ግብጽ ያስተናገደችውን 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና እ.አ.አ በ1998 በቡርኪናፋሶ የተካሄደውን 21ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ግብጽ ስታነሳ የቡድኑ አባላት ነበሩ። ወንድማማቾቹ የአፍሪካ ዋንጫን ሁለት ጊዜ በማንሳት ባለ ክብረ ወሰን ናቸው። የ59 ዓመቱ ሆሳም ሀሰን በአሁኑ ሰዓት የግብጽ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ነው። በተጫዋችነቱ በ177 ጨዋታዎች 69 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የምንጊዜውም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ነው። 3. አልበርት ባዋንጋ እና ሮበርት ካዛዲ (ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ)   ሁለቱ ወንድማማቾች ግብጽ እ.አ.አ በ1974 ባዘጋጀችው ዘጠነኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። በወቅቱ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ዛምቢያን በማሸነፍ ዋንጫውን ስታነሳ የታሪካዊው ድል አካል ነበሩ። 4. አንድሬ ካና ቢይክ እና ፍራንስዋ ኦማም ቢይክ (ካሜሮን)   ሁለቱ ወንድማማቾች በሶስት የአፍሪካ ውድድሮች ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። ተጨዋቾቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በአህጉራዊ መድረክ በጋራ የመሰለፍ እድል ያገኙት እ.አ.አ በ1988 በሞሮኮ አስተናጋጅነት በተካሄደው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው። እ.አ.አ በ1990 በአልጄሪያ በተካሄደው 17ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ሴኔጋል እ.አ.አ በ1992 ባዘጋጀችው 18ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። ጣልያን እ.አ.አ በ1990 ባዘጋጀችው 14ኛው የዓለም ዋንጫ ከወንድማማቾቹ ታናሹ ፍራንስዋ ኦማም ቢይክ ካሜሮን አርጀንቲናን 1 ለ 0 ባሸነፈችበት ጨዋታ ባስቆጠራት ጎል ሁሌም በሀገሬው ሰዎች ሲወሳ ይኖራል። 5. አንድሬ አየው እና ጆርዳን አየው (ጋና)   ጋናውያኑ ወንድማሞች የአፍሪካ ዋንጫ ሲነሳ ሁሌም የሚታወሱ ተጫዋቾች ናቸው። በስድስት የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ አብረው ተሰልፈዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ አብረው የሰለፉት ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን እ.አ.አ በ2012 ባዘጋጁት 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። የአየው ወንድማማቾች እ.አ.አ በ2015 ኢኳቶሪያል ጊኒ ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማንሳት ተቃርበው የነበሩ ቢሆንም በፍጻሜው በኮትዲቭዋር በመለያ ምት ተሸንፈው ህልማቸው ሳይሳካ ቀርቷል። የታዋቂው አፍሪካዊ ተጫዋች አብዲ ፔሌ ልጆች የሆኑት አንድሬ እና ጆርዳን አየው እ.አ.አ በ2023 በኮትዲቭዋር አስተናጋጅነት በተካሄደው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለመጨረሻ ጊዜ በጋራ ተሰልፈዋል። ጋና እ.አ.አ በ2008 ባዘጋጀችው 26ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጋናዊው አጥቂ አሳሞሃ ጊያን እና ታናሽ ወንድሙ ባፎር አንድ ላይ ተጫውተዋል። በተጨማሪም በዛው ውድድር ላይ ጋናውያኑ ወንድማማቾች ሪቻርድ ኪንግስተን እና ላሪያ ጊንግስተን አብረው የመጫወት እድል አግኝተዋል። 6. ኮሎ ቱሬ እና ያያ ቱሬ (ኮትዲቭዋር)   በአፍሪካ እግር ኳስ ውስጥ ስማቸው በግንባር ቀደምትነት ከሚነሱ ተጫዋቾች መካከል ኮሎ ቱሬ እና ያያ ቱሬ ይጠቀሳሉ። ወንድማማቾቹ ለመጀመሪያ ጊዜ አብረው የተሰለፉት እ.አ.አ በ2006 በግብጽ አስተናጋጅነት በተካሄደው 25ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በወቅቱ ኮትዲቭዋር ለፍጻሜ ደርሳ በግብጽ ተሸንፋለች። ኢኳቶሪያል ጊኒ እ.አ.አ በ2015 ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ኮትዲቭዋር ጋናን በማሸነፍ ዋንጫውን ለሁለተኛ ጊዜ ስታነሳ በጋራ የድሉ ተቋዳሽ ሆነዋል። የቱሬ ወንድማማቾች ለስድስት ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫው አብረው ተጫውተዋል። 7. የሞሪታኒያ እና ዛምቢያ ወንድማማች ተጫዋቾች   እ.አ.አ በ2023 ኮትዲቭዋር ባስተናገደችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሞሪታኒያ ብሄራዊ ቡድን ስብስብ ከሁለት ቤተሰብ በተመሳሳይ ሁለት ወንድማማቾች መሳተፋቸው የተለየ ትኩረት ስቧል። ኑህ መሐመድ አብድ እና ታናሹ ሲዲ መሐመድ አህመድ አብድ በተከላካይ እና አማካይ መስመር ላይ ተሰልፈው ተጫውተዋል። ላሚን ባ እና ኤል ሃጂ ባ ለሞሪታኒያ ብሄራዊ ቡድን በመሰለፍ መጫወት ችለዋል። ዛምቢያዊያኑ ክርስቶፈር እና ፍሊክስ ካቶንጎ እ.አ.አ በ2012 ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን በጣምራ ባዘጋጁት 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዛምቢያ ኮትዲቭዋር በማሸነፍ የአፍሪካ ዋንጫን ስታነሳ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል።   ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ2013 ባዘጋጀችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይም በጋራ ተሰልፈው ተጫውተዋል። ዛምቢያውያኑ ወንድማማቾች ኬኔት እና ሞርዶን ማሊቶሊ እ.አ.አ በ1994 በቱኒዚያ በተካሄደው 19ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ1996 ባዘጋጀችው 20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አንድ ላይ ተሰልፈዋል። አለን ትራኦሬ እና ኢብራሂማ ትራኦሬ (ቡርኪናፋሶ) በ30ኛው እና 31ኛው የአፍሪካ ፣ ሳምቡ ያታባሬ እና ሙስጠፋ ያታባሬ (ማሊ) በተመሳሳይ በ30ኛው እና 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ፒተር ንዶልቩ እና አዳም ንዶልቩ (ዚምባቡዌ) በ24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ሳሉ፣ ባቺሩ እና ታጁ (ቶጎ) በ22ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ቾሞጎ ኦማር እና ሴዲያት ኦማር (ቤኒን) በ24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ መሐመድ እና ሙሳ ካሎን (ሴራሊዮን) በ20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ሳሚር ሳሊሚና አዴል ሳሊሚ (ቱኒዚያ) በ19ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አብረው የተሰለፉ ተጫዋቾች ናቸው። በአፍሪካ ዋንጫ ከተሰለፉ ወንድማማቾች መካከል ስድስቱ የአፍሪካ ዋንጫን ማንሳታቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል።
የኢትዮጵያ እና የህንድ ዘመን አይሽሬ እና ድንበር  ተሻጋሪ ወዳጅነት 
Dec 16, 2025 989
በሙሴ መለስ (ኢዜአ) ኢትዮጵያ እና ህንድ ረጅም ክፍለ ዘመናትን ያስቆጠረ ወዳጅነት እና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት አላቸው። በዚህም የስልጣኔ እሴቶችን ይጋራሉ። ሁለቱ ሀገራት የንግድ ትስስር ከፈጠሩ ከ2000 ዓመታት በላይ እንዳስቆጠሩ የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ። የኢትዮጵያ እና ህንድ ዘመናዊ የዲፕሎማሲ ግንኙነት መሰረት የሀገራቱ ታሪካዊ ወዳሽነት እንደሆነም ይወሳል። ኢትዮጵያ እና ህንድ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1948 ነው። እ.አ.አ በ1950 ሳርዳት ሳንት ሲንግ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የህንድ አምባሳደር በመሆን ተሹመዋል። በወቅቱ ኢትዮጵያ እና ህንድ በየሀገራቱ ኤምባሲ በመክፈት የዲፕሎማሲ ትብብሩን ለማጠናከር ያላቸውን ቁርጠኝነት በተግባር ገልጸዋል። ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ እ.አ.አ በ1956 እና በ1958 በህንድ ያደረጓቸው ጉብኝቶች ከኢትዮጵያ መሪዎች ጉብኝቶች በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው። እ.አ.አ 1960 ዎቹ ማብቂያ እና 1970ዎቹ መጀመሪያ ላይ የህንድ ፕሬዝዳንቶች የነበሩት ሳርቬፓሊ ራድሃክሪሽናን እና ዛኪር ሁሴን በኢትዮጵያ የስራ ጉብኝቶችን አድርገዋል። እ.አ.አ በ2011 ከአንድ ዓመት በፊት ህይታቸው ያለፈው የቀድሞው የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ማንሞሃን ሲንግ በኢትዮጵያ ያደረጉት የስራ ጉብኝትም ተጠቃሽ ነው። የቀድሞው የህንድ ፕሬዝዳንት ራም ናት ኮቪንድ እ.አ.አ በ2017 የስራ ጉብኝት ያደረጉ ሲሆን በወቅቱ በጉብኝታቸው ህንድ እና ኢትዮጵያ በንግድ፣ ኮሙኒኬሽን እና የሁለትዮሽ ትብብር ማጠናከር የሚያስችሉ የጋራ መግባቢያ ስምምነቶችን ተፈራርመዋል። ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ2023 ባዘጋጀችው 15ኛው የብሪክስ የመሪዎች ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከነበራቸው ተሳትፎ ጎን ለጎን ከህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አድርገዋል። የሀገራቱ መሪዎች በወቅቱ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በመከላከያ፣ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በግብርና፣ የወጣቶች ክህሎት ማጎልበት እና በሕዝብ ለሕዝብ ልውውጥ ዙሪያ ትብብርን በማጠናከር ዙሪያ ተወያይተዋል። በወቅቱ ህንድ ባዘጋጀችው የሁለተኛው “Voice of Global South Summit” በተሰኘው ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ተሳትፎ አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ2016 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንደራ ሞዲ በህንድ አጠቃላይ ምርጫ ለሶስተኛ ጊዜ ማሸነፋቸውን ተከትሎ የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክት አስተላልፈውም ነበር። የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንደራ ሞዲም የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)ን የደስታ መግለጫ መልዕክት በመቀበል በአዲሱ የስልጣን ዘመናቸው ህንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት አጋርነት እንደሚያድግ መግለጻቸውም ይታወሳል። ህንድ እና ኢትዮጵያ በአፍሪካና በደቡብ ደቡብ ትብብር ያላቸውን አጋርነት ጠቅላይ ሚኒስትሩ አንስተዋል። በዚህም ህንድ ከኢትዮጵያ ጋር ላላት የሁለትዮሽ ትብብር ከፍተኛ ትኩረት እንደምትሰጥም ነበር ጠቅላይ ሚኒስትር ሞዲ ያስታወቁት። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው 20ኛው የቡድን 20 አባላት ሀገራት ጉባኤ ከነበራቸው ተሳትፎ ጎን ለጎን ከህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ጋር ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ትርጉም ያለው እና ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውንም ገልጸዋል። ህንድ የቡድን 20 አባል ሀገር መሆኗ የሀገራቱን የባለብዙ ወገን ትብብር የበለጠ የሚያጠናክር ነው። ከእ.አ.አ 2021 እስከ 2024 ባለው ጊዜ ውስጥ ሀገራቱ የሁለትዮሽ እና የባለዙወገን ትብብራቸውን የሚያጠናክሩ ተከታታይ ውይይቶችን አድርገዋል። በወቅቱ የህንድ የትምህርት፣ ንግድ፣ ልማት፣ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሮች በኢትዮጵያ ያደረጓቸው ጉብኝቶች የሀገራቱ ግንኙነት የበለጠ እየጠነከረ መምጣቱን የሚያሳዩ ናቸው። ህንድ ኢትዮጵያ የብሪክስ አባል እንድትሆን ድጋፍ ያደረገች ሲሆን በብዝሃ ወገን ማዕቀፉ ሁለቱ ሀገራት በትብብር እየሰሩም ይገኛሉ። ኢትዮጵያ እና ህንድ በተለያዩ ጊዜያት በአየር ትራንስፖርት፣ ኢኮኖሚ፣ ኢንቨስትመንት፣ መከላከያ፣ ተደራራቢ ታክስን የማስቀረት፣ ንግድ፣ ኮሙኒኬሽን ሳይንስ፣ባህል፣ ትምህርት እና የጋራ ሚኒስትሮች ኮሚሽን ማቋቋምን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች መስራት የሚያስችሏቸው የሁለትዮሽ ስምምነቶችን ተፈራርመዋል። እ.አ.አ ፌብሩዋሪ 2025 ኢትዮጵያ እና ህንድ በመከላከያና ደህንነት ዘርፍ የተፈራረሙት የሁለትዮሽ ስምምነት ቁልፍ የሚባል ነው። እ.አ.አ በ2023/24 በወጣ መረጃ የኢትዮጵያ እና ህንድ የሁለትዮሽ የንግድ ልውውጥ ምጣኔ 271 ሚሊዮን ዶላር ደርሷል። ኢትዮጵያ አተር፣ ቅመማ ቅመሞች፣ የቆዳ ውጤቶች እና የከበሩ ድንጋዮችን ወደ ህንድ ትልካለች። ከህንድ ደግሞ ማሽነሪዎች፣ የመድኃኒትት ምርቶች እና የብረታ ብረት ውጤቶችን በዋናነት ታስገባለች። ህንድ የኢትዮጵያ ዋንኛ የኢንቨስትመንት አጋር ከሚባሉ ሀገራት መካከል ትጠቀሳለች። ከ500 በላይ የህንድ ኩባንያዎች በጨርቃ ጨርቅ፣ ግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግ እና አገልግሎት ዘርፎች ተሰማርተው ይገኛሉ። ህንድ መሰረተ ልማቶችን ጨምሮ ለኢትዮጵያ ግዙፍ ፕሮጀክቶች የፋይናንስ አቅርቦት ታደርጋለች። ንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ትምህርት፣ ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ኢኖቬሽን፣ ጤና እና መሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ከሁለቱ ሀገራት አበይት የትብብር መስኮች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው። የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ በኢትዮጵያ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ለማድረግ ዛሬ ማምሻውን አዲስ አበባ ገብተዋል። ሞዲ በኢትዮጵያ ጉብኝት ሲያደርጉ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ከማንሞሃን ሲንግ በኋላ ኢትዮጵያን የጎበኙ ሁለተኛው ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት ህንድ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከአፍሪካ ጋር ያላትን የልማት አጋርነት ማሳደግን ያለመ ነው። የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ በኢትዮጵያ ቆይታቸው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጨምሮ ከሌሎች የመንግስት ባለስልጣናት ጋር ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አባላት በፓርላማ ተገኝተው ንግግር እንደሚያደርጉ የጉብኝታቸው መርሃ ግብር ያሳያል። የሁለቱ ሀገራት መሪዎች ተከታታይ የሁለትዮሽ ውይይቶች እና የጉብኝት ልውውጦች የኢትዮጵያ እና የህንድን ግንኙነት የበለጠ የሚያጸኑ ናቸው። ኢትዮጵያ እና ህንድ በታዳሽ ኃይል፣ ፋርማሲዩቲካል፣ ዲጂታል ቴክኖሎጂ እና ግብርና ማቀነባበሪያን ጨምሮ በአዳዲስ መስኮች ትብብራቸውን የማጠናከር ጽኑ ፍላጎት አላቸው። የሁለቱ ሀገራት ትብብር ከእርስ በእርስ ግንኙነት ባለፈ የአፍሪካ እና ህንድ እንዲሁም የደቡብ ደቡብ ትብብር ማሳያ ሆኖ የሚጠቀስ ነው። ከ2000 ዓመት በፊት የተጀመረው የሀገራቱ ወዳጅነት ወደ ጠንካራ እና ጽኑ ትብብር ተቀይሯል። በማይናወጥ መሰረት ላይም ቆሟል። የበለጠ ጥልቀቱ እየጨመረ የመጣው የሀገራቱ ግንኙነት በጋራ ብልጽግና፣ ስትራቴጂካዊ ትስስር፣ ዘላቂ ልማት እና የሀገራቱን ዜጎች ተጠቃሚ ባደረገ መልኩ አጠናክሮ ለመቀጠል የጋራ ቁርጠኝነቱ ከመቼውም ጊዜ በላይ ጨምሯል።  
በአረንጓዴ ልምላሜ ያጌጠው - የቤንቾች ቀዬ
Dec 3, 2025 1329
በአረንጓዴ ልምላሜ ያጌጠው - የቤንቾች ቀዬ (በቀደሰ ተክሌ) -ከሚዛን ቅርንጫፍ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የሚገኘው የቤንች ምድር የሰጡትን የሚያበቅል ክረምት ከበጋ የማይጠወልግ ልምላሜን የታደለ ክልል ነው። በቤንች ሸኮ ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች ደን የሚመስልና በመኖሪያ መንደሮች የሚታየው አብዛኛው አረንጓዴ ስፍራ ለምግብነት የሚያገለግሉ ፍራፍሬዎች፣ ቅጠሎችና ስሮችን የያዘ ነው። የቤንቾች ቤት ዙሪያው በአረንጓዴ ተፈጥሮ ያጌጠ ነው። የቤታቸው ሞገስ፤ የምግብ ዋስትናቸውም ጭምር ነው። ከዚህ ከፍ ሲል ደግሞ ቤንቾች ነፋሻማ አየር እየማጉ የመኖር ልምድን ያጎናጸፋቸው ይኸው አፈር ቆፍረው ዘር ተክለው ያበቀሉትና የተንከባከቡት አረንጓዴ ሀብት ነው። ከአንድ አርሶ አደር ማሳ እንሰት፣ ሙዝ፣ ጎደሬ፣ ፓፓያ፣ አቮካዶ፣ ብርቱካን እና ሌሎች ፍራፍሬዎች ማየት የተለመደ ነው።   እግር ጥሎት ወደ ቀዬያቸው ያመራ እንግዳ ከፍራፍሬዎቹ የደረሰ ካለ ተቆርጦ ይሰጠዋል። በተጨማሪም ከብቶች፣ በጎችና ዶሮዎች የገቢ ምንጮቻቸው ናቸው። ወደ ቤታቸው ዘልቆ የገባ ሰው "ኪዥ" የተሰኘና የቤንች እናቶች ከወተት የሚያዘጋጁትን ''ጎደሬ'' ተብሎ ከሚጠራ የስራ ስር ምግብ ጋር ያጣጥማል። ቤንቾች በቆሎ፣ ማሽላ፣ ስንዴ፣ ባቄላ እንዲሁም ሌሎች የሰብል ዓይነቶችን ያለማሉ። ማር፣ ቡና፣ ኮረሪማ እና ሌሎች የተፈጥሮ ቅመማ ቅመሞችም ቤንቾች ከገበያ ገዝተው የሚያመጡት ሳይሆን ከማሳቸው የሚያፈሩት ነው። የተቀናጀ እርሻን ባህል ያደረጉት ብርቱ የቤንች አርሶ አደሮች ወደ ገበያ አውጥተው የሚሸጡት እንጂ የሚገዙት የለም ቢባል ማጋነን አይሆንም። የፋብሪካ ውጤቶችን ለመግዛትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግም ከጓዳቸው ሞልቶ የተረፈውን ወደ ገበያ አውጥተው በመሸጥ ገበያን ያረጋጋሉ። በጠንካራ የእርሻ ባህላቸውም ምክንያት ልጆቻቸው የበሰለ ምግብን ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ፍራፍሬዎችንም ከጓሮና ከጫካ ቆርጠው ስለሚመገቡ ረሀብን አያውቁም።   የቤንቾች ቤት ዙሪያ ውብና ጽዱ ነው። ለዚህ ደግሞ ሴቶቹ የቤታቸውን ግድግዳ በተፈጥሮ ቀለም ከማስዋብ ጀምሮ ይጠበቡበታል። በቤንቾች ዘንድ የአንድ አርሶ አደር ጉብዝና የሚለካው በቤቱ ነው። ይህም የቤቱ ዙሪያ ያለው ውበትና የቤቱ ጥንካሬ ብቻም ሳይሆን ገላጣ መሆን አለመሆኑም ጭምር ከግምት ውስጥ ይገባል። አባዎራው በማሳው ላይ የሰብል ስራውን ያከናውናል። ልጆችና እማውራዋ ደግሞ ይኮተኩታሉ ያርማሉ። ከዚህም በተጨማሪ የቤንች እናት ጎደሬና ሌሎች የጓሮ አትክልቶችን የማልማት ኃላፊነት አለባት። የቤታቸው ዙሪያና ቀዬው በሙሉ በአረንጓዴ ልምላሜ አጊጦ የሚታይበት ምስጢሩ ይሄው ነው። ከርቀት ደን መስሎ የሚታየው አረንጓዴው ቀዬአቸው የገቢ ምንጭም በመሆኑ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ነውም ማለት ይቻላል። የሌማት ትሩፋት እሳቤ ቀድሞ የገባቸው ቤንቾች ማር አይገዙም፤ ለእንቁላል ሸመታም ገበያ አይወጡም። ወተት ቢያምራቸው በትኩሱ፤ ከዛም አለፍ ሲል በባህላዊ መንገድ እርሾ ጨምረው የሚያዘጋጁት "ኪዥ" የተሰኘ የወተት ውጤትን እንደ አይብም እንደ እርጎም አደርገው ይጠቀሙታል። የትኛውንም መልክዓ ምድር በሚስማማው የሰብል ዓይነት መሸፈን ያውቁበታል። መሬቱ ረግረጋማ ከሆነ ለጎደሬ፤ ዳገታማ ሆኖ ለማረስ የሚያስቸግር ከሆነ ደግሞ ለሙዝ ልማት ያውሉታል።   የምግብ ዋስትናን በቤተሰብ ደረጃ ለማረጋገጥ ሥራ የሚሠራው በጓሮ ነው። ይህም ሁሉን ከአንድ ጓሮ ለማግኘት በመጣር የሚመጣ ነው። ይህም ካልሆነ ደግሞ አስተማማኝና ቋሚ ምርት ማሳ ላይ አልያም ጎተራው ላይ ማኖር ያስፈልጋል። እንደ ቤንቾች በቤተሰብ ደረጃ ምግብን በራስ አቅም ለመቻል የሚደረገው ጥረት እንደሀገር ሲጠናከር ለውጡ ቀጣይነት ባለው መልኩ ይፋጠናን። ሀገራችን ኢትዮጵያ ካላት የሕዝብ ቁጥር አብዛኛው አርሶ አደር ነው። ይሁን እንጂ ጾሙን የሚያድር ሰፊ መሬት እንዳለ መረጃዎች ያመለከታሉ። አንድም መሬት ጾም እንዳያድር በየአካባቢው ስራዎች ቢጀመረም ውጤቱ ቀሪ ሥራዎችን የሚጠይቅ ነው። ዛሬም በምርት እጥረት የኑሮ ውድነትና መሰል ችግሮች ይስተዋላሉ። በእነዚህ መሬቶች ላይ ሰርቶ ከመለወጥ ይልቅ ከተማ ቁጭ ማለትን የሚሻ ትውልድ ማየት የተለመደ ነው። የቤንች ሸኮ ዞን አርሶ አደሮች እጃቸው ብርቱ በመሆኑ እነዚህ ችግሮች በስራ አሽንፈዋል። ይህም በምግብ ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ በኢኮኖሚም እንዲረጋጉ አድርጓቸዋል።   ለሀብት ምንጭ የሆነን ማሳ ለቆ ከተማ በመዋል የሚገኝ ነገር አይኖርም። በከተማም ሆነ በገጠር ለመለወጥ እንደ ቤንቾች ብርቱ እጆች ያስፈልጋሉ። ካልተሰራ ገቢ ሳይሆን ወጪ እያደገ ወዳልተገባ መንገድ ለመሄድ ምክንያት ይሆናል። ለችግርም ሆነ ሰርቶ የመለወጥ ዕድሉ የሚወሰነው በምርጫችንና ለሥራችን በምንሰጠው ትኩረት ነው። እንደ ቤንች ሸኮ ዞን አርሶ አደሮች ሰርቶ ለመለወጥና ራስን ለመቻል በየአካባቢው ያለን የተፈጥሮ ሀብት ወደ ልማት ለመቀየር ተግቶ መስራት ያስፈልጋል ። ሰላም!
ብልህ ከችግር ይማራል!!
Dec 2, 2025 855
ብልህ ከደረሰበት ችግር ይማራል!! በማሙሽ ጋረደው ገራድ ተስፋዬ ተፈራ ትውልድና እድገታቸው በሀድያ ዞን ሌሞ ወረዳ ቃልሻ ቀበሌ ሲሆን በ1999 ዓ.ም በህገ ወጥ መንገድ ከፍተኛ ገንዘብ አውጥተው ወደ ደቡብ አፍሪካ ተጉዘው እንደነበር ያስታውሳሉ። ገንዘብ ለማግኘትና የመለውጥ ህልማቸውን ለማሳካት በሚል ሩቅ አስበው የጀመሩት ህገ ወጥ ጉዞ መዳረሻውን እስር ቤት አደረገው። ይህም ሁኔታ ''ሩቅ አሳቢ-ቅርብ አዳሪ'' አደረጋቸው። በባዕድ አገር በነበራቸው የ2 ዓመት የእስር ቤት ቆይታም የምግብ እጦትን ጨምሮ አካላዊ ጥቃትና ጉልበት ብዝበዛ እንዲሁም የተለያዩ ስነ-ልቦናዊ ጉዳቶችን እንዳስተናገዱ ይናገራሉ።   ይህም አልበቃ ብሎ ከአካባቢው በህገወጥ መንገድ የሚሰደዱ ወጣቶችን ጉልበት በመጠቀም ሰፋፊ እርሻዎች ላይ እንዲሰማሩ በማድረግ የጉልበት ብዝበዛ ይፈፀምባቸው እንደነበርም ያስታውሳሉ። ብልህ ከደረሰበት ችግር ይማራል! የሚሉት ገራድ ተስፋዬ ሩቅ ሳይጓዙ፣ ገንዘብ ሳያወጡ ሰርተው መለወጥ የሚችሉበትን አካባቢያቸውን ፀጋ ሳያማትሩ ስደት መሄዳቸው ቁጭት ፈጥሮባቸው ነበር፡፡ ይህም በሀገራቸው እንኳንስ የለማን መሬት ይቅርና የተቦረቦረ መሬትን አልምቶ ጉልበትንና ጊዜን በአግባቡ ተጠቅሞ ለስኬት መብቃት እንደሚቻል ከእስር ቤት ቆይታቸው ተምረው ከእስር እንደተፈቱም ወዲያውኑ ወደ ሀገር ቤት መመለሳቸውን ተናግረዋል። በ2001 ዓ.ም ወደ ሀገር ቤት እንደተመለሱም በማህበር ተደራጅተው ከመንግሥት ባገኙት 70 ሺህ ብር ብድር በእንስሳት እርባታ ላይ ለመሰማራት 4 የወተት ከብቶችን ገዝተው የእርባታ ስራ መጀመራቸውን ይገልጻሉ፡፡   በዚህም የዞኑ አስተዳደር የሰጣቸውን መሬት አልምተው የእንስሳት እርባታውን አስፋፍተው መስራት ጀመሩ፡፡ አሁን ላይ የወተት ላሞቹን ቁጥር 37 በማድረስ የወተት ምርታማነታቸው አድጎ ከቤት ፍጆታ አልፎ ለሆሳዕና ከተማና አካባቢው በቀን ከ670 ሊትር በላይ ወተት እያቀረቡ ይገኛሉ፡፡ ለ40 ወጣቶችም ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል ከመፍጠራቸውም ባሻገር የተለያዩ የጭነትና የስራ ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ ከ250 ሚሊዮን ብር በላይ ሀብት ማፍራት መቻላቸውን ይናገራሉ። የጀመሩትን ስራ በጥምር ግብርና የማስፋትና የሚያገኙትን ወተት በማቀነባበር ምርቱን በተለያየ መልኩ ለገበያ የማቅረብ ራዕይን ሰንቀው በትጋት እየሰሩ ይገኛሉ፡፡ በህገወጥ ስደት ካጋጠማቸው ችግር ተነስተው በተግባር ያዩትን ለሌሎች በማስተማር የስደትን አስከፊነት ለአካባቢያቸው ወጣቶች እያስገነዘቡ መሆኑን ገልጸዋል።   ወጣቶች የስደትን አማራጭ ከመመልከታቸው በፊት የአካባቢያቸውን ፀጋ እንዲቃኙና ራዕይ ሰንቀው ራሳቸውን ለማሻሻል እንዲሰሩም መክረዋል። መለወጥ በውጪ ሀገር ብቻ ያለ የሚመስላቸው የቤተሰብ ኃላፊዎችም ልጆቻቸው በሀገራቸው ሰርተው መለወጥ እንደሚችሉ በማመን ሊያግዟቸው እንደሚገባም አቶ ገራድ አስገንዝበዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትልና የእርሻና ሆርቲካልቸር ዘርፍ ኃላፊ አቶ አለምይርጋ ወልደስላሴ፤ በክልሉ በርካታ ወጣቶች ያልተጨበጠ ተስፋ ሰንቀው ለህገወጥ ስደትና ለተለያዩ ችግሮች ተጋላጭ እየሆኑ ይገኛሉ ብለዋል፡፡   በሀገር ሰርቶ ለመለወጥ የሚያስችል አቅም በግብርናው ዘርፍ መኖሩን ጠቅሰው በዘርፉ የተሰማሩ ከስደት ተመላሾች በአካባቢያቸው ሰርተው ለስኬት እየበቁ እንደሚገኙም ጠቁመዋል፡፡ በዚህም ከራሳቸው አልፈው ለበርካታ ስራ አጥ ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር ላይ የሚገኙና የእነዚህን አካላት ተሞክሮ በመውሰድ በሀገር ሰርቶ ለመለወጥ መትጋት ይገባል ብለዋል፡፡
ዲጂታል ግብርና፤ የአፍሪካ ግብርና አዲስ ምዕራፍ
Dec 1, 2025 555
ዲጂታል ግብርና በጥቅሉ ሲተረጎም የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን ለግብርና ስራዎች መጠቀም ማለት ነው። ቴክኖሎጂዎቹ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ፣ የገበያ ተደራሽነትን በማስፋት፣ በአቅርቦት የእሴት ሰንሰለት ላይ መጠናከር፣ በቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት፣ የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምና የአየር ንብረት ለውጥ አይገበገሬነት ስራዎችን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አላቸው። የዓለም የዲጂታል ግብርና ገበያ እ.አ.አ በ2022 ከ10 እስከ 12 ቢሊዮን መድረሱን የተለያዩ መረጃዎች ያመለክታሉ። እ.አ.አ በ2028 የገበያ መጠኑ ከ23 እስከ 25 ቢሊየን ዶላር እንደሚደርስ ትንበያ ተቀምጧል። የዲጂታል ግብርና በአውሮፓ፣ በሰሜን አሜሪካ እና እስያ ፓሲፊክ በፍጥነት እያደገ ሲሆን በአፍሪካና ላቲን አሜሪካ ጅምር ላይ ነው ማለት ይቻላል። ሰሜን አሜሪካ 40 በመቶ እና አውሮፓ 25 በመቶ የዓለም የዲጂታል ግብርና ገበያ ድርሻን ይይዛሉ። አርሶ አደሮች ለዲጂታል ግብርና የሚያስፈልጋቸውን ቴክኖሎጂዎችን አለማግኘት፣ የዳታ ደህንነት እና የግል መረጃ ጥበቃ፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የኢንተርኔት ተደራሽነትና ባህላዊ ልማዶችን ከዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ጋር ማስተሳሰር ዓለም አቀፍ የዘርፉ ፈተናዎች ናቸው።   አፍሪካ ከአምስት እስከ ሰባት በመቶ(ከ500 እስከ 800 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር) የሚገመት ነው። በአፍሪካ የግብርና ቴክኖሎጂ ያለው ኢንቨስትመንት በፍጥነት እያደገ ይገኛል። ዘርፉ ከ400 ሚሊየን ዶላር መዋዕለ ንዋይ ፈሶበታል። በሞባይል የማማከር አገልግሎት፣ የገበያ ትስስር ማዕቀፎችና ለአርሶ አደሮች የፋይናንስ ቴክኖሎጂዎች ተደራሽ የማድረግ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። የቴክኖሎጂዎቹ የተደራሽነትና አላምዶ የመጠቀም ውስንነት፣ የመሰረተ ልማት ግንባታ፣ የፖሊሲ እና የህግ ማዕቀፍ እክሎች እንዲሁ አካታችነት የአፍሪካ ፈተናዎች ናቸው። በአፍሪካ አብዛኛው ግብርና በአነስተኛ ይዞታ ባላቸው አርሶ አደሮች ላይ የተመሰረተ ሲሆን ግብርና ለአፍሪካውያን ኑሮ እና የምግብ ዋስትና ወሳኝ የሚባል ነው። በዚህ ረገድም የዲጂታል ግብርና ለግብርና ምርታማነት ማደግ፣ የአቅርቦት እጥረትን በመቅረፍና የልማት ግቦች በማሳካት ረገድ የበኩሉን ሚና ይጫወታል። ኢትዮጵያ ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት በጥር ወር 2017 ዓ.ም የዲጂታል ግብርና ፍኖተ ካርታ ይፋ አድርጋለች። በወቅቱ የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ከግብርና ሚኒስቴር እና የጌትስ ፋውንዴሽን ጋር በመሆን ፍኖተ ካርታውን በጋራ ይፋ አድርገዋል። ማዕቀፉ ከዚህ ቀደም የነበሩ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴንሽንና ማማከር አገልግሎቶች በአንድ ጥላ ስር ያስቀመጠ ነው። ፍኖተ ካርታው የግብርና እሴት ሰንሰለቱን በሙሉ ዲጂታላይዝ የማድረግ አላማ አለው። የማማከርና የፋይናንስ አገልግሎቶች፣ የገበያ መረጃ፣ ዲጂታል ክህሎት፣ ሜካናይዜሽን፣ የዳታ መረጃ አሰባሰብና ዲጂታል መሰረተ ልማት የፍኖተ ካርታው አበይት ትኩረቶች ናቸው።   መንግስት ከልማት አጋሮች ጋር በመሆን የዲጂታል ግብርናን ለማስፋት እየሰራ ነው። የአፍሪካ ህብረት ያዘጋጀው የመጀመሪያው የዲጂታል ግብርና ጉባኤ በአዲስ አበባ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል። “ኢኖቬሽን እና የዲጂታል መፍትሄዎችን ለግብርና ዘርፍ በመጠቀም የአፍሪካን መጻኢ ጊዜ ብሩህ ማድረግ” የጉባኤው መሪ ሀሳብ ነው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊካ ሃዳዲ በጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር ኅብረቱ ዲጂታላይዜሽንን የልማት አጀንዳው አድርጎ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የግብርናው ዘርፍም በዚህ የዲጂታላይዜሽን አህጉራዊ ስትራቴጂ ውስጥ ትኩረት እንደተሰጠው አንስተዋል። ኮሚሽኑ አባል ሀገራት ለዲጂታል ግብርና የመረጃ አጠቃቀምና አስተዳደር አመቺ ፖሊሲዎችን እንዲያዘጋጁ እና እንዲተገብሩ ድጋፍ ያደርጋል ነው ያሉት። ለአርሶ አደሮች፣ ለግብርና ባለሙያዎችና ለወጣቶች በዲጂታል ክህሎቶች ዙሪያ ሥልጠና እንደሚሰጥም አረጋግጠዋል። በአፍሪካ ዲጂታል ግብርናን እውን ለማድረግ የአባል ሀገራት መንግስታት፣ የልማት አጋሮች፣ የግሉ ዘርፍ ተዋናዮች እና የምርምር ተቋማት በቅንጅት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።   የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ በበኩላቸው የአፍሪካን የግብርና ሥርዓት ለመለወጥ እና የምግብ ዋስትናን በዘላቂነት ለማረጋገጥ ዲጂታል ግብርናን መተግበር የግድ ነው ብለዋል። ዲጂታል ግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ የምርት ብክነትን ለመቀነስ፣ የፋይናንስና የገበያ ተደራሽነትን ለማስፋት እንዲሁም የመቋቋም አቅምን ለመገንባት ቁልፍ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ወጣቶች የአፍሪካ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ለኢኖቬሽንና ለዲጂታል ግብርና ትኩረት እንዲሰጡ ጠይቀዋል። ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ ትራንስፎርሜሽን ለማምጣት ዲጂታል ግብርናን እንደ ቁልፍ ስልት መውሰዷንና ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ዘርፉን ለማዘመን የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ በመድረኩ የተገኙት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ኢፋ ሙለታ(ዶ/ር) ገልጸዋል። የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎትን በስማርት ስልኮች አማካይነት ተደራሽ ማድረግ፣ ትክክለኛ የግብርና መረጃዎችን በአንድ ቋት መያዝና ማዘመን ላይ እየተሰራ መሆኑንና የግብርና ግብዓትን ተደራሽ ማድረግ፣ ከማሳ እስከ ገበያ ባለው ሂደት ውስጥ ያሉ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት ለማጎልበት ዲጂታላይዜሽን ላይ መሰራቱንም ጠቅሰዋል። የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ፣ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴሽን አገልግሎት፣ የግብርና ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን፣ የገበያ ተደራሽነት፣ የእሴት ሰንሰለትን ማጠናከር፣ የግብርና ምርታማነትን ከአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም መገንባት ጋር ያስተሳሰረ አካሄድን መከተል፣ የግብርና ፖሊሲዎችና የህግ ማዕቀፎች ትግበራ የኮንፍረንሱ ተሳታፊዎች የሚመክሩባቸው አጀንዳዎች ናቸው። ኮንፍረንሱ የእውቀት ሽግግር እና ፖሊሲ ተኮር ውይይቶች የሚደረግበት ሲሆን ስኬታማ የሀገራት የግብርና ኢኒሼቲቮች ለተሳታፊዎች ይቀርቡበታል። በአፍሪካ የዲጂታል ግብርና መፍትሄዎችን ተደራሽነት የሚደግፉ ስትራቴጂዎች የመለየት እና አጋርነቶችን ማጠናከር ከሁነቱ የሚጠበቅ አበይት ውጤት መሆኑን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የኢንተርኔት ተደራሽነት በሚፈለገው መጠን አለማደግ ፣ የዲጂታል ክህሎት ማነስ፣ የመሰረ ልማት ግንባታ እና የፖሊሲ ማዕቀፍ የዘርፉ ፈተናዎች ሲሆኑ ለአፍሪካ የዲጂታል ግብርና ትሩፋቶች ከፈተናዎቹ ይገዝፋሉ። ዲጂታል ግብርና ለአፍሪካ ዘላቂ ልማት፣ የምግብ ዋስትና መረጋገጥ እና ኢኮኖመሚ ልማት አንቀሳቃሽ ሞተር የመሆን አቅም አለው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም