ቀጥታ፡
መጣጥፍ
ቱሪዝም- የኢትዮጵያ የማከናወን ዐቅም ማሳያ
Jun 29, 2026 3774
በዮሐንስ ደርበው “ሀገራችን ከቱሪዝም ልታገኛቸው የምትችላቸውን ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና አካባቢያዊ ጥቅሞች ሁሉ ከቀረው ዓለም ጋር ተወዳድራ እንድታገኝ፣ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ጎብኚ ወደ ሀገራችን መሳብ አለብን። ለዚህም የተለያዩ ስልታዊ መላዎች ነድፈን እየተንቀሳቀስን እንገኛለን (የመደመር መንግሥት 273)። የቱሪዝም ኢንዱስትሪ የለውጡ መንግሥት እመርታዎችን ካስመዘገበባቸው ዘርፎች አንዱ ነው። መንግሥት ከአምሥቱ የትኩረት መስኮች አንዱ አንድርጎም በጥናት፣ አካባቢያዊ ፀጋን ዐውቆና ለይቶ በተደመረ ዐቅም ባከናወናቸው ሥራዎች በገበታ ለሸገር፣ በገበታ ለሀገር፣ በገበታ ለትውልድ፣ በኮሪደር ልማት፣ በወንዝ እና የወንዝ ዳርቻዎች ልማት እሠየው ያሰኙ ተግባራት አከናውኗል። የብርቱዎቹ ልጆች ብርታት በቀጣይ ...! በገበታ ለሸገር የተገለጠው የተደመረ ዐቅም - ለኢትዮጵያ ስኬቶች እንደማሳያ የመልከ መልካሟ ብዙ መልኮች ለአስም በሽታ አጋላጭ ምክንያቶችና ሊደረጉ የሚገባቸው ጥንቃቄዎች በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው ከእንጦጦ - ቀበና የተከናወነው የወንዝና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክትም ለጎብኚም ለነዋሪም ምቹ ከባቢን በመፍጠር ረገድ እየተደረገ ያለውን ትጋት ያስረዳል። ምረቃውን ተከትሎ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ባጋራው መረጃ፤ “መቆሸሽ እኛ አይገባንም፣ መጠልሸት እኛ አይገባንም፣ ማነስ እኛ አይገባንም! ሠርተን እንደምንችል ማሳየት ያስፈልጋል” ሲል የሥራውን ማራኪነትና ውበት ገልጿል። ጠቅላይ ሚኒስትሩም በዚሁ ወቅት፤ ‎የተሰጠንን ሕዝባዊ አደራ በታማኝነት፣ በጽኑ ትጋት እና በቅንነት በመፈጸም የዜጎቻችንን የኑሮ ጥራት ለማሻሻልና መሠረታዊ ለውጥ ለማምጣት የጀመርነውን ጉዞ አበክረን እንቀጥላለን ሲሉ በቀጣይ ካለፈው የበለጠ እንደሚሠራ አመላክተዋል። ገንዘብን፣ ዕውቀትን፣ ጉልበትን፣ ሐሳብን፣ የአመራር ብቃትን ስንደምር የሚከሰተው ነገር እንደዚህ ያለው ውበት ይሆናል ሲሉም አስገንዝበዋል። በመደመር መንግሥት መጽሐፋቸው (ገጽ 256) ላይም፤ “የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ሀገራት በዘመናቸው ሁሉ የሠሩትንና ተፈጥሮ ያደለቻቸውን መልካም ገጽታ በኩራት ለዓለም የሚያስተዋውቁበት፣ ‘ሀገሬ ይሄንን ትመስላለች’ የሚሉበት መድረክ ነው። ሀገርን በሚያኮራና ለሌሎች ለመጋበዝ በማያሳፍር መልኩ መገንባት፣ ለቱሪዝም ኢንዱስትሪ መሠረቱ ነው።” ያሉትም የበለጸገች ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ በቁጭት መነሳታቸውን ይገልጻል። ነገን ዛሬ እየሠራች ያለችው ኢትዮጵያ ካላት ላይ ሳትነፍግ የገንዘብም ሆነ የሰው ኃብቷን ቱሪዝም ላይ ስታውል፤ አንድም የኢንዱስትሪውን ዐዋጭነት ብሎም የዜጎቿን በየዘርፉ ዘላቂ ተጠቃሚነት በመገንዘብ ነው። እዚህ ላይ ለሀገር ገቢ በማስገኘት እና የሥራ ዕድል በመፍጠር ዘርፉ የሚያበረክተውን ጥቅም ማጤን ይገባል። በአዲስ አበባ ከተከናወኑ ቁልፍ የቱሪዝም ልማቶች መከካከል፤ የመስቀል ዐደባባይ ቅርስን ማንበርና ማዘመን፣ ከአዲስ አበባ ልማት ጋር ተሣሥሮ የተገነባው የዓድዋ ድል መታሰቢያ፣ በአዲስ መልክ የታደሠው ብሔራዊ ቤተ-መንግሥት፣ የአምሥቱ ዕውቀት ተኮር ማዕከላት (አብርኾት ቤተ-መጻሕፍት፣ ሳይንስ ሙዝየም፣ የሀገር በቀል ዕጽዋት ማሳያ፣ የአንድነት ቤተ-መዛግብት እና የማዕድን ሙዝየም) ግንባታ፣ የአዲስ አበባ ኮንቬንሽን ማዕከል እና ሌሎችም ይገኙበታል። በሌላ በኩል ደግሞ ጎብኚዎች የሚያርፉበት ሎጂና ሆቴሎች ግንባታም በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። ገበታ ለሸገር ብሎ ከአዲስ አበባ የተነሳው የቱሪዝም ልማት በገበታ ለሀገርና ገበታ ለትውልድ ወደ ክልሎች ተስፋፍቶ ደረጃቸውን የጠበቁ ሎጂዎች እንዲገነቡ አስችሏል። የተገነቡት ሎጂዎች ደግሞ ለጎብኚዎቹ ምቾትን የሚያስጠብቁ መሠረተ-ልማቶችን ስበዋል። በርካታ ጎብኚ መሳብና ገቢን ማሳደግ፣ በጎ ገጽታን መሸጥ፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር፣ የበለጸገች ኢትዮጵያ ዕውን ማድረግ እየተከናወኑ ላሉ ተግባራት ሁሉ ግቦች ናቸው። መንግሥት ዕምቅ የጎብኚዎች መስኅብ ዐቅም የሆኑና አቧራ ለብሰው የተደበቁትን ፀጋዎች ውበታቸውን ገላልጦ እያሳዬ ያለውም ለዚህ ነው። ቱሪዝም በቀጥታ ዜጎች (ሰዎች) የሚጠቀሙበት ኢንዱስትሪ ነው። ለዚህ ደግሞ ሰዎች ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠርና መጠበቅ ይኖርባቸዋል።መሠረተ-ልማቶችን በመጠበቅ እንዲሁም ከመንግሥት ጎን በመሆን በሚፈለጉበት ሁሉ ንቁ ተሳትፎ ማድረግም ይጠበቅባቸዋል። ዜጎች ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ቁርጠኝነታቸውን ያረጋገጡበት ጠቅላላ ምርጫ ምክክር - ወደ መግባባት መሻጋገሪያው ድልድይ! ያልተቋረጠ የስኬት ጉዞ #የኢትዮጵያ_ዜና_አገልግሎት #Ethiopian_News_Agency #ቱሪዝም #PMOEthiopia #በኢዜአ_ዐይን #PMOEthiopia #EthiopiaDelivers
ኢትዮጵያ ያሸነፈችበት - የሕዝብ ድምጽ
Jun 26, 2026 2905
ኢትዮጵያ ያሸነፈችበት - የሕዝብ ድምጽ ኢትዮጵያ በዴሞክራሲ ፍኖቷ ለአፍሪካ አርአያ ሆና አሳይታለች... የአፍሪካውያን ቀንዲል ናት። የክፉ ቀን መሸሸጊያቸው፣ የመከራ ጊዜ መጽናኛቸው፣ የነጻነት ተምሳሌትና የጥቁር ሕዝቦች ኩራት የሆነችው ኢትዮጵያ፣ በረጅም ዘመናት ታሪካዊ መስተጋብር የተፈጠረ የሀገረ መንግሥት መዋቅር ባለቤት ናት። በተፈጥሮ ጸጋዎች፣ ምድሯን ሰንጥቀው በሚያልፉ ወንዞቿ የምትታወቅ አገር ናት። የተለያዩ ማዕድናት በብዛት የሚገኙባት ከመሆኗም በላይ፣ የበርካታ ብሔረሰቦች ባህልና እሴቶች ሕብር ሠርተው፣ ተስማምተው የሚኖሩባት የታሪክ ማህደር ናት። ይሁን እንጂ ይህ ታሪካዊ ግርማ ሞገስና የነጻነት አርማነት፣ በውስጣዊ የፖለቲካ ጉዞዋ ውስጥ ካጋጠሟት መዋቅራዊ ስብራቶችና የሥልጣን ፍትጊያዎች ሊታደጋት አልቻለም። ለዘመናት በሀገሪቷ የሰፈነው የሥልጣን ሥርዓት የሰፊውን ሕዝብ ፍላጎትና ተሳትፎ ያገለለ፣ በጥቂት የሕብረተሰብ ክፍሎችና ልሂቃን ፍላጎት ላይ ብቻ የተመሠረተ ነበር። ይህ አካሄድ በሀገሪቱ ታሪክ ውስጥ አንዱን ሥርዓት በሌላው እየተካ፣ የተተካው አገዛዝ ደግሞ የባሰ ጭቆናን ይዞ የሚመጣበትን አዙሪት ፈጥሯል። ከብዙ መቶ ዓመታት የዘውድ አገዛዝ በኋላ የመጣው ወታደራዊ ሥርዓት፣ በመቀጠልም ለ30 ዓመታት ገደማ የዘለቀው የአንድ ወገን የበላይነት የሰፈነበት አብዮታዊ ዴሞክራሲ ሀገሪቱንና ዜጎቿን ለከፍተኛ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ዳርገው አልፈዋል። ይህ ዓይነቱ የመከራና የጭቆና ሰንሰለት ግን በ2010 ዓ.ም በተቀጣጠለው ሀገራዊ ለውጥ ተገርስሶ ወደ አዲስ የፖለቲካና የዴሞክራሲ ምሕዳር ተሸጋግሯል። ያለፉትን ስምንት ዓመታት የኢትዮጵያን የፖለቲካ ጉዞ ስንመረምር፣ ሀገሪቷ ከአሮጌውና ከተለመደው የአፈና ሥርዓት ወጥታ አዲስ የዴሞክራሲ ሥርዓት ለመገንባት ቁርጠኛ አቅም ይዛለች። ይህ ወቅት የዜጎች የፖለቲካ ተሳትፎ መብት በተግባር የተረጋገጠበትና የሐሳብ ብዝኃነት የተስተናገደበት ምዕራፍ ነው። ከዚህ ቀደም የሥልጣን ማራዘሚያ ሆነው ያገለግሉ የነበሩ ዋና ዋና ተቋማት ገለልተኛና ነፃ ሆነው እንዲደራጁ መደረጉ የለውጡ ትልቁ ስኬት ሆኖ ሊጠቀስ ይችላል። በዚህ የሽግግር ሂደት ውስጥ የለውጡ የመጀመሪያ ፍሬ የታየው በ2013 ዓ.ም የተካሄደው ስድስተኛው ምርጫ ነበር። በወቅቱ የነበሩትን ሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ተቆቁሞ ሕዝቡ ያሳየው የባለቤትነት ስሜት የዴሞክራሲ ናፍቆቱን በግልጽ ያሳየ ነው። ይህንን ተሞክሮ መሠረት በማድረግ፣ በዘንድሮው የ2018 ዓ.ም የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የኢትዮጵያ ሕዝብ ይበልጥ የነቃ አስደናቂ የፖለቲካ ተሳትፎ አሳይቷል። ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም የተካሄደው ይህ ታሪካዊ መድረክ፣ የኢትዮጵያ ዜጎች ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ያላቸውን የማይናወጥ አቋም አሳይተውበታል። ከንጋት እስከ እኩለ ሌሊት ረጅም ሰዓታትን ተሰልፈው የተፈጥሮ የአየር ንብረት ተጽዕኖዎችንና ልዩ ልዩ ፈተናዎችን በሙሉ በትዕግሥት በመሻገር ድምፃቸውን ሰጥተዋል። ይህ ሂደት የሚያሳየው ሕዝቡ የሥልጣን ምንጭነቱን በተግባር የተረዳበትና ልዩነቶችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የወሰነበት ትልቅ ምዕራፍ መሆኑን ነው። በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ዘንድ የኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ጉዞና የውስጥ መረጋጋት ሁልጊዜም በከፍተኛ ትኩረት የሚከታተሉት ጉዳይ ነው። ላለፉት ዓመታት በተለያዩ ዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ የሚነሱ ሥጋቶችና የጂኦፖለቲካ ጫናዎች ቢኖሩም፣ ይህ በስኬት የተጠናቀቀው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የሀገሪቷን የውስጥ ጥንካሬና ሉዓላዊነት በተግባር ያስመሰከረ ሆኗል። በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች በነፃነትና በሰላም ድምፅ የሰጡበት ይህ ሂደት፣ ኢትዮጵያ የራሷን የውስጥ ጉዳይ በራሷ ዜጎች ፍላጎት የመወሰን ሙሉ አቅም እንዳላት ለዓለም አሳይቷል። ምርጫው ከሁሉ በላይ ኢትዮጵያ ያሸነፈችበት ታላቅ ታሪካዊ ክስተት ነው። ሕዝቡ በነቂስ ወጥቶ ድምፁን በመስጠት የሀገሩን ሉዓላዊነትና አንድነት አስከብሯል። የፖለቲካ ሥልጣን የሚገኘው በጠመንጃ አፈሙዝ ወይም በሁከት ሳይሆን በሕዝብ የላቀ ውሳኔ ብቻ መሆኑን በማረጋገጥ፣ ሀገራችን ካለፈችባቸው የፖለቲካ ስብራቶች በላይ ከፍ ብላ እንድትቆም አድርጓታል። ይህ ደግሞ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረኮች ያላትን ተደማጭነትና የድርድር አቅም ከፍ የሚያደርግ ነው። የምርጫው ዝርዝር ስኬቶች ምን ምን ናቸው የሚለውን ስንመለከት፦ 👉የአፈሙዝ ድምፅንና የጽንፈኛ ዛቻን ያሸነፈው የሕዝብ ጽናት ግንቦት 24 ታሪካዊ ቀን ናት። በዚህች ታሪካዊ ዕለት፣ በየምርጫ ጣቢያው በነቂስ ወጥቶ ድምፁን የሰጠው ሕዝብ ያሳየው የነጻነት፣ የሉዓላዊነት እና የጽናት ማረጋገጫ ነው። ምርጫውን ለማደናቀፍና ሕዝቡን ለማስፈራራት የተቃጡ የአፈሙዞች ድምፆችና የሁከት ዛቻዎች ነበሩ፤ ነገር ግን ሕዝብ ከመምረጥ አላፈገፈገም። መራጮች የጽንፈኛ ኃይሎችን ዛቻ ወደ ጎን ትተው፣ የአካላቸውን ሕመም፣ የበሽታን ሥቃይ፣ አልፎ ተርፎም የወሊድ ምጥንና የቅርብ ዘመድ ሞት ያመጣውን ጥልቅ ሐዘን በሕሊናቸውና በሥጋቸው ተሸክመው ነበር ረጅሙን ሰልፍ ተሰልፈው ይበጀኛል ያሉትን በካርዳቸው የመረጡት። ይህ የሚያሳየው እውነት ለኢትዮጵያውያን የምርጫ ካርድ ሰላማቸውን የሚገዙበት፣ መብታቸውን የሚያስከብሩበትና የወደፊት ዕጣ ፈንታቸውን በገዛ እጃቸው የሚወስኑበት ብቸኛ የነጻነት አዋጃቸው መሆኑን ነው። ሕዝቡ ከምርጫ ውጭ በሆነ መንገድ፣ በኃይል ወይም በሁከት ሥልጣን ለመያዝ ምኞትና የቆየ የሥልጣን ናፍቆት ላላቸው ወገኖች በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ግልጽና የማያሻማ መልዕክት አስተላልፏል። የኢትዮጵያ ሕዝብ የኃይልና የሁከት አካሄድን እንደማይቀበል፣ በድምፅ ላይ ብቻ የተመሠረተ ሕጋዊ ሥርዓትን ለማፅናት እንደሚታገል አረጋግጧል። ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ይህን ጉዳይ በተመለከተ በአፅንኦት ሲያነሱ፤ "የዘመናችን ዲሞክራሲ አስተምህሮቱ ሰላምና ዕድገት፣ ቋንቋው ደግሞ መምረጥና መመረጥ ብቻ በመሆኑ የፖለቲካ ቅኝታችሁንና አካሄዳችሁን ከዚሁ ስልጡን መስመር ጋር ማስተካከል ይበጃችኋል። ካሁን በኋላ የሕዝብ ድምፅ ያልጎበኘው፣ የምርጫ ካርድ ያልዳሰሰው የፖለቲካ ሥልጣን መያዣ መንገድ በኢትዮጵያ ዝግ መሆኑን እነሆ እንዳየነው መሠረት የጣለ ስለሆነ ይህኑ ስልጡን መንገድ ለመቀበል የማትፈቅዱ ሁሉ ግን ግፋ ቢል የዘመናችን የፖለቲካ ድርሳን ሲጻፍ ልትሆኑ የምትችሉት የግርጌ ማስታወሻ ብቻ ነው።" ብለዋል። ስለሆነም ከዴሞክራሲያዊ፣ ሰላማዊና ሕጋዊ አካሄድ ውጭ የሚደረግ ሙከራ የጥፋት ተዋናይ ከመሆን ባሻገር ለሀገር የሚያተርፈው አንዳች ነገር እንደሌለ በዚህ ስሑት መንገድ ላይ የሚገኙ አካላት ሊገነዘቡ ይገባል። 1. ምርጫው በቁጥሮች ሲገለጽ የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በጉልህ የሚጠቀሱ አኃዛዊ መረጃዎች አሉት። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ተስፋዬ ንዋይ እንደገለጹት፤ ቦርዱ ከ120 ሚሊዮን በላይ የድምፅ መስጫ ወረቀቶችን በውጭ ሀገር አሳትሞ ካስመጣ በኋላ፣ ከምርጫው 4 ቀናት በፊት በሀገሪቱ ባሉት ከ52 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የምርጫ ጣቢያዎች በታማኝነትና በጥንቃቄ ማድረስ ተችሏል። ይህንን እጅግ ግዙፍና ውስብስብ የሎጂስቲክስ ሥራ ሙሉ በሙሉ ያከናወኑት የቦርዱ ኢትዮጵያውያን ሠራተኞች ብቻ መሆናቸው ተቋማዊ አቅሙ ምን ያህል እንደጎለበተ ማሳያ ነው። የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ እንደተናገሩት፤ የቦርዱ ሠራተኞችና የምርጫ አስፈጻሚዎች በዕረፍት ቀናትና በሌሊት በመጋዘን ውስጥ ጭምር እያደሩ የቁሳቁስ ማሸግ ሥራዎችን በትጋት አከናውነዋል። ሩቅና ተደራሽነታቸው አስቸጋሪ በሆኑ አካባቢዎች ደግሞ ቁሳቁሶችን በእግር፣ በእንስሳት ጀርባና በጀልባ ጭምር በማጓጓዝ፣ ወንዞችን ለመሻገር የራሳቸውን የፕላስቲክ ጀልባ ሠርተው ሀገራዊ አደራቸውን ተወጥተዋል። በድምፅ መስጫ ቀን ሥራቸውን ከንጋት እስከ ንጋት በልዩ ብርታት ፈጽመዋል። ይህ ልብ የሚነካ እውነታ የሚያሳየው፣ የዴሞክራሲ ተቋማት ግንባታና የሕዝብ ድምፅ እንዲከበር የሚደረገው ጥረት ከፍተኛ ዋጋ ያለው የተናጥልና የጋራ ትጋት የሚጠይቅ መሆኑን ነው። ሰፊ ተሳትፎ፦ 42 የፖለቲካ ፓርቲዎችና 80 የግል ዕጩዎች ተሳትፈዋል። 10 ሺህ 438 የፖለቲካ ፓርቲና የግል ዕጩዎች ተወዳድረዋል። ቦርዱ ለመጀመሪያ ጊዜ ፓርቲዎች ፖሊሲዎቻቸውን ለሕዝብ የሚያስተዋውቁበት የክርክር መድረክ ያዘጋጀ ሲሆን፤ ይህ ተግባር ፓርቲዎች ከምርጫው ውጭም ራሳቸውን ለሕዝብ የሚያቀርቡበትን ባህል ያዳብራል። የመራጮችና አስፈጻሚዎች ቁጥር፦ በአጠቃላይ 54 ሚሊዮን 57 ሺህ 861 መራጮች የተመዘገቡ ሲሆን፤ ምርጫውን ለማስፈጸም ከ350 ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያን ተሳትፈዋል። ታዛቢዎችና ወኪሎች፦ ከ260 ሺህ በላይ የፖለቲካ ፓርቲ ወኪሎች፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ያሰማሯቸው ከ60 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥ ታዛቢዎች፣ እንዲሁም 63 የአፍሪካ ኅብረት እና 26 የኢጋድ ታዛቢዎች ተሳትፈዋል። ለመራጩ ሕዝብ የሥነ ዜጋና የመራጮች ትምህርት ለመስጠት መስፈርቱን ላሟሉ 169 ሀገር በቀል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ፈቃድ ተሰጥቷል። እንዲሁም 21 ሚሲዮኖችና አንድ የውጭ ሀገር የምርጫ አስፈጻሚ ተቋም ምርጫውን ተመልክተዋል። የአየር ሰዓት አጠቃቀም፦ የፖለቲካ ፓርቲዎችና የግል ዕጩዎች ነፃ የአየር ሰዓት የማግኘት መብት ስለነበራቸው ለሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ 752.5 ነፃ የሬዲዮ ሰዓት፣ 57.5 ነፃ የቴሌቪዥን ሰዓትና 576 የጋዜጣ ኮለምን በዘመናዊ የዕጣ ማውጣት ሥርዓት ተደልድሎ እንዲጠቀሙ ተደርጓል። መገናኛ ብዙኃን፦ 73 የሀገር ውስጥና የውጭ መገናኛ ብዙኃንን የወከሉ 1 ሺህ 827 የሀገር ውስጥና 45 የውጭ ጋዜጠኞች ለዘገባ ሥራ ተሰማርተዋል። የሕግ ማሻሻያ እና ዲጂታላይዜሽን፦ አዋጅ ቁጥር 1162/2011 ተሻሽሎ በአዋጅ ቁጥር 1394/2017 ተተክቷል። ቦርዱ 10 አዳዲስ መመሪያዎችን አጽድቋል። የፖለቲካ ፓርቲዎች ክርክር፦ ለመጀመሪያ ጊዜ በገለልተኛ ባለሙያዎች የሚመራ፣ እያንዳንዳቸው 2 ሰዓት የሚወስዱ 19 የክርክር መድረኮች በቦርዱ ተዘጋጅተዋል። 14ቱ በአማርኛ፣ 5ቱ በክልል ቋንቋዎች (አፋን ኦሮሞ፣ ሶማሊኛ፣ ሲዳምኛ፣ አፋርኛ) ተካሂደው በሰባት መገናኛ ብዙኃን በፕራይም ታይም ተላልፈዋል። አካታችነት፦ 28 ሺህ 632 የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮችና ከ20 ሺህ በላይ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ጨምሮ ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች በልዩ የምርጫ ጣቢያዎች እንዲመዘገቡ ተደርጓል። የቅሬታ አፈታትና ክትትል፦ የቅድመ አደጋ ማሳወቂያ ሥርዓት (Early Warning System) ተዘርግቷል። 663 የምርጫ ክልል ቅሬታ ሰሚ ኮሚቴዎችና ልዩ የአጣሪ ጉባኤ ተደራጅተው 129 አቤቱታዎችን መርምረዋል። የሕግ ጥሰት በተገኘባቸው ጣቢያዎች ውጤት እንዲሰረዝ እና በፈጻሚዎች ላይ አስተዳደራዊና የወንጀል ተጠያቂነት እንዲኖር ተወስኗል። 2. ጠንካራና ገለልተኛ ተቋም፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የሀገር ውስጥ አቅም ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም የተካሄደው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ መጠነ ሰፊ ተቋማዊና ሕጋዊ ማሻሻያዎች የተደረጉበት ከመሆኑም በላይ፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር ረገድ ሀገራዊ አቅምን በተግባር ያሳየ ነበር። የዚህ ምርጫ ትልቁ ትርፍ ጠንካራና የማይናወጡ ብሔራዊ ተቋማትን መገንባት መቻላችን ነው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያሳየው ፍጹም ገለልተኝነት፣ የሕግ የበላይነትን የማስከበር ብቃት እና የቴክኖሎጂ ሽግግርን በሀገር ውስጥ ባለሙያዎች የመተግበር አቅም፣ ተቋማት ከግለሰቦችና ከፖለቲካ ጫና በላይ መሆናቸውን ያስመሰከረ ነው። ይህም ለቀጣዩ ትውልድ የሚሻገር አስተማማኝ የመንግሥት መዋቅር መሠረት ነው። ለምርጫው ስኬት ግንባር ቀደም ተጠቃሽ የሆነው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ነው። በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ መራጮችን በትዕግሥት በማስተናገድ፣ ብቁ አስፈጻሚዎችን በማሰማራትና ሂደቱን በታማኝነት በመምራት ረገድ ቦርዱ አድናቆት የተቸረው ሥራን ፈጽሟል። የሠራተኞቹ ቀንና ሌሊት መትጋት እንዲሁም በግንባር ቀደምትነት የሚመሩት አመራር አባላት ያሳዩት ቁርጠኝነት የላቀና ለሀገር ኩራት የሆነ ተግባር ነው። በዚህ ምርጫ ውስጥ ትልቁን ትኩረት የሳበውና ለመጀመሪያ ጊዜ በሥራ ላይ የዋለው የዲጂታል የመራጮች ምዝገባ ሥርዓት ነው። ይህ ዘመናዊ አሠራር ለምርጫው ከተመዘገቡ ከ54 ሚሊዮን በላይ መራጮች መካከል ከ5 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ወደ ምርጫ ጣቢያዎች በአካል መጓዝ ሳይጠበቅባቸው፣ ባሉበት ቦታ ሆነው በነፃነት እንዲመዘገቡ ዕድል ፈጥሯል። ቴክኖሎጂው የመራጮችን ማንነት በፎቶግራፍ ጭምር በማረጋገጡ በድምፅ መስጫ ቀን ሊፈጠሩ የሚችሉ ግድፈቶችንና ማጭበርበሮችን በከፍተኛ ደረጃ መከላከል ተችሏል። የዚህ ሥርዓት ዋነኛውና ትልቁ ድል ደግሞ ሙሉ በሙሉ ወጣት ኢትዮጵያውያን የቴክኖሎጂ ባለሙያዎች የበለጸገ መሆኑ ነው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ የዚህን የቴክኖሎጂ ስኬት አስፈላጊነት ሲያብራሩ፤ "እነዚህ የዲጂታል የምዝገባ ሥርዓቶች በውጭ ሀገር አገልግሎት አቅራቢ ድርጅቶች የለሙ ሳይሆን በራሳችን ወጣት ኢትዮጵያውያን የቴክኖሎጂ ባለሙያዎች የተገነቡ ናቸው። ይህም ተቋሙን ከውጭ አቅራቢዎች ጥገኝነት ነፃ በማድረግ በራሱ አቅም እንዲቆምና ለወደፊቱ ማሻሻያዎችን በራሱ እንዲያከናውን መሠረት ጥሏል።" ይህ እርምጃ ቦርዱ የውጭ የቴክኒክ ጥገኝነትን በመቀነስ የሀገር ውስጥ አቅምን ለመገንባትና የሉዓላዊነትና የደኅንነት ዋስትናን በራስ ቴክኖሎጂ ለማረጋገጥ የቻለበትን ስትራቴጂካዊ አካሄድ በግልጽ ያሳያል። በተጨማሪም በስድስተኛው ጠቅላላ ምርጫ በውጭ ዜጎች ይሠራ የነበረው የቴክኒክ ድጋፍ በአሁኑ ወቅት ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያውያን ሠራተኞች መተካቱ የተሳካ የእውቀት ሽግግር መኖሩን አሳይቷል። 3. ሕጋዊ ማሻሻያዎች፣ አካታችነትና ተጠያቂነት ዴሞክራሲ እውነተኛ ትርጉም የሚኖረው ዜጎች፣ በተለይም ሴቶችና አካል ጉዳተኞች ያለ ፍርሃትና ጫና፣ ደኅንነታቸው ተጠብቆ በፖለቲካዊ ሂደቶች እኩል መሳተፍ ሲችሉ ነው። ይህንን እውን ለማድረግ የሲቪል ማኅበራት ድርጅቶች ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል። ለምሳሌ የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማኅበር በታዛቢነት በመሳተፍ፣ ሴቶች የዴሞክራሲያዊ መብቶቻቸውን በነፃነት እንዲጠቀሙና በሂደቱ በንቃት እንዲሳተፉ አስችሏል። ቦርዱ የሴቶችን መብት ከማስከበር ባለፈ፣ ጾታዊ ጥቃትና ትንኮሳን ለመከላከል የሚያስችል ፖሊሲ ቀርጾ ተግባራዊ አድርጓል። ከዚህም በላይ በምርጫ ወቅት በሴቶች ላይ የሚደርሱ ጥቃቶችን ለመከላከልና ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል ግብረ ኃይል ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ለመጀመሪያ ጊዜ አቋቁሟል። በተጨማሪም የምርጫውን ግልጽነትና ተዓማኒነት ለማረጋገጥ ቀድሞ የነበረው አዋጅ ቁጥር 1162/2011 በአዋጅ ቁጥር 1394/2017 እንዲተካ የተደረገ ሲሆን፣ ቦርዱ ይህንን መነሻ በማድረግ 10 አዳዲስ መመሪያዎችን አጽድቋል። በነዚህ ማሻሻያዎች ውስጥ የሴቶችና የአካል ጉዳተኞችን ተሳትፎ ማሳደግ እንደ ዋና መርህ የተወሰደ ነው። 4. ፈተናዎችን መጋፈጥና ገለልተኝነትን ማስከበር ይህ ሁሉ ስኬት ግን ያለ ፈተና አልመጣም። ምርጫው በተያዘለት ጊዜ አይካሄድም የሚሉ ጥርጣሬዎችና የተሳሳቱ መረጃዎች ተቋሙን ፈትነውት ነበር። ሆኖም ቦርዱ ጫናዎችን በመቋቋም ሕግና መርህን ብቻ ተከትሎ በመሥራት ምርጫውን ለስኬት ማብቃቱን ወይዘሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ ያረጋግጣሉ። ቦርዱ በምርጫው ወቅት የተቋሙን ነፃነት ከማንኛውም ዓይነት ጫናና ጣልቃገብነት በመጠበቅ በሕግና በመርህ ላይ ተመሥርቶ ውሳኔዎችን ሲያሳልፍ ቆይቷል። በምርጫ አፈጻጸም የአሠራር ግድፈቶች እና ከፖለቲካ ፓርቲዎች የቀረቡ ቅሬታዎችን በመመርመር በአንዳንድ የምርጫ ክልሎች በድምፅ መስጫው ቀን ጭምር አስፈጻሚዎችን አሰናብቷል፤ በምርጫ ውጤቶች ላይም ውሳኔ ሰጥቷል። ይህም ቦርዱ ለሕግ የበላይነትና ለምርጫ ታማኝነት ያለውን ጽኑ አቋም ያሳያል። የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ስኬት በአንድ ተቋም ወይም በጥቂት ግለሰቦች ብቻ ሳይሆን በሚሊዮን የሚቆጠሩ መራጮች በፀሐይና በዝናብ ሳይበገሩ በትዕግሥት የሰጡት ድምፅ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የጸጥታ አካላት፣ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ታዛቢዎች (እንደ አፍሪካ ኅብረትና ኢጋድ) እንዲሁም የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት የጋራ ጥረት ውጤት ነው። 5. የምርጫው ግልጽነትና ዓለም አቀፍ እውቅና የምርጫውን ታሪካዊ ሂደትና ተዓማኒነት ለማረጋገጥ የሀገር ውስጥና የውጭ አካላት በሰፊው ተሳትፈዋል። ሂደቱን ለመዘገብ 73 ለሚሆኑ የሀገር ውስጥና የውጭ መገናኛ ብዙኃን ፈቃድ የተሰጠ ሲሆን፣ በአጠቃላይ 1 ሺህ 827 ጋዜጠኞች የዘገባ ሥራቸውን አከናውነዋል። ከ260 ሺህ በላይ የፖለቲካ ፓርቲ ወኪሎች እና ከ64 ሺህ በላይ ሀገር በቀል የሲቪል ማኅበራት ታዛቢዎች በሂደቱ ላይ ተሳትፈዋል። በተለይም በምርጫ ቦርድ ዕውቅና የተሰጣቸው 55 የሀገር በቀል የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች 60 ሺህ 277 ታዛቢዎችን በማሰማራት ሂደቱን የተከታተሉ ሲሆን፤ 169 ድርጅቶች ደግሞ ለመራጮች የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት ሰጥተዋል። በአህጉር ደረጃም የኬንያ የቀድሞው ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የሚመሩትና ከ60 በላይ ታዛቢዎችን ያቀፈው የአፍሪካ ኅብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን እና 26 የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነመንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ታዛቢዎች ሂደቱን በታዛቢነት ተከታትለዋል። ዓለም አቀፍ ታዛቢዎች ምርጫው ግልጽ፣ አሳታፊና ተዓማኒ ሆኖ በስኬት መካሄዱንም አረጋግጠዋል። 👉የአፍሪካ ህብረት እና የኢጋድ ታዛቢ ቡድኖች ምስክርነት የአፍሪካ ህብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪ የኬንያ የቀድሞ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ በሰጡት መግለጫ፣ የምርጫው ዕለት ሰላማዊ፣ ሥነ ሥርዓት የሰፈነበት እና ግልፅነት የታየበት መሆኑን ነው ያረጋገጡት። በቴክኖሎጂ የታገዘ የመራጮች ምዝገባ መተግበሩ ወጣቶችን መሳቡን፣ ዜጎች በትዕግሥት ሰልፍ በመያዝ ጥልቅ ፍላጎታቸውን ማሳየታቸውን፣ የሎጂስቲክስ ዝግጅቱ የተሟላ መሆኑንና የምርጫ ሰዓት መራዘሙ የሚደነቅ መሆኑን ጠቁመዋል። በመስተንግዶ ረገድም ወንበሮችና የምግብ አቅርቦቶች መኖራቸው ረጅሙን ሰልፍ ታጋሽ እንዳደረገውና ለአረጋውያንና አካል ጉዳተኞች ቅድሚያ መሰጠቱን አረጋግጠዋል። የቀድሞ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ለኢትዮጵያውያን ባስተላለፉት መልዕክት "ቅኝ ግዛትን በአንድነት የተከላከለች Couch፣ ለአፍሪካ ነፃነት የቆመች እና የአህጉሪቱ ዋና ከተማ በሆነች ሀገር ውስጥ የተደረገው ይህ ምርጫ ትልቅ ምዕራፍ በመሆኑ ኢትዮጵያውያን በታሪካቸው ሊኮሩ ይገባል፤ ወደፊት ለመራመድም በሕዝቦች መካከል ያለውን የፖለቲካ እና የማኅበረሰብ ውይይት ይበልጥ ማሳደግ፣ ወደ ኋላ የተተዉ የሚሰማቸውን አካላት ወደ መድረኩ በማምጣት እና አካታችና የተባበረች ኢትዮጵያን መገንባት ያስፈልጋል" ብለዋል። በሌላ በኩል፣ የኡጋንዳ የቀድሞ ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ስፔሲዮዛ ዋንዲራ ካዚብዌ የሚመራው የኢጋድ (IGAD) የምርጫ ታዛቢ ቡድን በሰባት ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች 28 ጣቢያዎችን በመጎብኘት የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርቱን አውጥቷል። ቡድኑ ጣቢያዎቹ በሰዓታቸው መከፈታቸውን፣ በቂ ቁሳቁስና አስፈጻሚዎች እንደነበሩ፣ የሳጥኖች አስተሻሸግ የድምፅ ምስጢራዊነትን ያረጋገጠ መሆኑንና የድምፅ አሰጣጡ ያለምንም መሰናክል በጥሩ ሁኔታ መካሄዱን በመታዘብ ምስክርነቱን ሰጥቷል። ለአረጋውያን፣ ሕፃናት ለያዙ ሴቶችና አካል ጉዳተኞች ቅድሚያ መሰጠቱንና መራጮች የሚቀመጡባቸው ወንበሮች መኖራቸውን የጠቀሰው ሪፖርቱ፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምርጫውን በማዘጋጀትና በመምራት ረገድ ከፍተኛ አስተዳደራዊና ኦፕሬሽናል አቅም ማሳየቱን አጉልቷል። የኢጋድ የምርጫ ታዛቢ ቡድን ለሰላማዊና ተዓማኒ ምርጫ የተደረገውን የጋራ ቁርጠኝነት ያደነቀ ሲሆን፣ "ይህ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በኢትዮጵያ ዲሞክራሲያዊ እና ምርጫ ዕድገት ላይ በተለይም የምርጫ አስተዳደርን ለማሻሻል፣ አካታችነትን እና ተዓማኒነትን ለማሳደግ የተነደፉ ዋና ዋና ቴክኖሎጂያዊ እና ተቋማዊ ማሻሻያዎች የተስተዋሉበት ትልቅ ምዕራፍ ነው" ሲል ቡድኑ ምስክርነታቸውን በአፅንኦት የገለጹት። የአፍሪካ ኅብረት የፖለቲካ ጉዳዮች፣ የሰላምና ደኅንነት ኮሚሽነር አምባሳደር ባንኮሌ አዶዬ "ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ታሪክ ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የከፈተ ነው። በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሥርዓት ይበልጥ እንዲጠናከርና ቀጣይነት ያለው መሻሻል እንዲመዘገብ አብረን ለመሥራት ያለንን ጽኑ ቁርጠኝነት እናረጋግጣለን።" ሲሉ ነው የተደመጡት። 6. የምርጫው ውጤት፣ የሕዝቡ ጽናትና የአሸናፊው ፓርቲ ከባድ ሸክም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰኔ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ይፋ ባደረገው ውጤት መሠረት፣ ብልፅግና ፓርቲ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 438 መቀመጫዎችን በማግኘት አሸንፏል። በሌላ በኩል ተፎካካሪ ፓርቲዎችና የግል ዕጩዎችም በምክር ቤቶቹ ወንበሮችን ማግኘት የቻሉ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) 13፣ የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ ስድስት፣ ነጻነትና እኩልነት ፓርቲ ሦስት፣ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ ሦስት፣ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይል ንቅናቄ ሦስት፣ ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ሁለት ወንበሮችን አሸንፈዋል። በሌላ በኩል ኦብነግ፣ ጉህዴን፣ አርጎባ አንድነት ጀበርቲ፣ የአፋር ሕዝብ ፓርቲ፣ የወላይታ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ግንባር፣ አዲስ ትውልድ ፓርቲ፣ የሶማሌ ፌዴራሊስት ፓርቲ፣ ኅብረት ለዴሞክራሲና ለነጻነት፣ ሰላም ለኢትዮጵያ ጥምረት፣ የጌዴዮ ሕዝብ ዴሞክራሲያዊ ድርጅት እያንዳንዳቸው አንድ ወንበር ሲያገኙ 8 የግል ተወዳዳሪዎችም ምክር ቤት ለመግባት አሸንፈዋል። ይህን ሰባተኛውን ጠቅላላ ምርጫ ከሌሎች ጊዜያት ለየት የሚያደርገው ታላቅ ክስተት፣ መራጩ ሕዝብ በታጋሽነት ተሰልፎ የመምረጥ መብቱን ለመጠቀም ያሳየው ወደር የለሽ ጽናት ነው። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህ ይህንን የሕብረተሰብ አደራ "አሸናፊው ፓርቲ ትልቅ ሀገራዊ ሸክም የተጣለበት መሆኑን ብልፅግና ፓርቲ በሚገባ ይረዳል። ፓርቲያችን በማኒፌስቷችንና በአጠቃላይ በምርጫ ቅስቀሳችን ወቅት ለሕዝብ ቃል የገባናቸውን በተግባር ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት ይንቀሳቀሳል" ብለዋል፡፡ 👉የፉክክርና የትብብር ሚዛን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ምሕዳር በቀጣይነት ሊመራበት የሚገባው ስልጡን መስመር በፉክክርና በትብብር መካከል ያለውን ሚዛን ጠብቆ መጓዝ ነው። ብልፅግና ፓርቲ ከሌሎች ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎችና በሀገር ግንባታ ላይ ሚና ካላቸው አካላት ጋር በብሔራዊ ጥቅም ላይ በትብብር ለመሥራት ያለው አቋም የጸና መሆኑን የፓርቲው ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህ በሰጡት አስተያየት፤ "ባለፉት ዓመታት የጀመርነውን በፉክክርና በትብብር መካከል ሚዛን ጠብቆ የሚሄድ ጥረታችንን በቀጣይ አጠናክረን የምንቀጥል ይሆናል። በምንሠራቸው ሥራዎች ሁሉ ሕዝቡን በማሳተፍ፣ በየጊዜው የሕዝቡን ግብረ መልስ በመስማት፣ ያንን እንደ ግብዓት ተጠቅመን የእቅድ አካል አድርገን ወደ ተግባር ለመተርጎም በቁርጠኝነት እንንቀሳቀሳለን።" ብለዋል። ይህ ዕይታ የኢትዮጵያ ፖለቲካ የሕዝብን ድምፅና ግብረ መልስ በየጊዜው የሚያዳምጥ፣ እንዲሁም ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ለሀገር ጥቅም በጋራ የመሥራትን ስልጡንና አካታች የአሠራር ሥርዓት መከተል መጀመሩን ያሳያል። 7. ዴሞክራሲና ምርጫው የሚገለጽባቸው አራቱ ምሰሶዎች ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ማለት አማራጭ የሌለው የህልውና ጉዳይና የሁለንተናዊ ብልጽግናችን መሠረት ነው። ብዝኃነትን በአግባቡ ማስተናገድ፣ ዘላቂ ሰላምን ማረጋገጥና ጠንካራ ሀገር መገንባት የሚቻለው በዴሞክራሲያዊ ምሰሶዎች ላይ በመመሥረት ብቻ ነው። መንግሥት ለዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ሲሠራ ቆይቷል። በዚህ ሂደት ውስጥ የሲቪል ማኅበራት ሚና የማይተካና አዎንታዊ ሚና አላቸው። መራጩን ሕዝብ ከማስተማር፣ ሕገ መንግሥታዊ የመምረጥ መብቱን እንዲጠቀም ከማስቻል፣ እስከ ሰላም እሴት ግንባታና በመንግሥትና በሕዝብ መካከል ድልድይ በመሆን የዜጎችን ባለቤትነት ከማረጋገጥ አኳያ የላቀ አስተዋጽኦ አበርክተዋል። የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ እንደገለጹት፣ የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ስኬት በአራት ዋና ዋና ምሰሶዎች ላይ የቆመ ነው። አንደኛው ምሰሶ፦ ምርጫ የሰላም ዋስትና መሆኑን መረዳት ነው። ሕዝቡ ልዩነቶችን በፀብና በአምባጓሮ ከመፍታት አዙሪት ተላቆ፣ በሰላማዊ መንገድ የመሻገር ባህልን መርጧል። በነቂስ ድምፁን መስጠቱ ኋላ ቀር የአመፃ መንገድን ለሚከተሉ ሁሉ "በቃችሁ" የሚል መልዕክት ያስተላለፈበት ሲሆን፣ የሰፊው ሕዝብ ማዕበላዊ ድምፅ ከአሮጌው የብጥብጥ ባህል መላቀቅ እንደሚፈልግ ማረጋገጫ ነው። ሁለተኛው ምሰሶ፦ የምርጫ ውግንና ከሕዝብ ጋር መሆኑን ማወቅ ነው። የምርጫ ተዓማኒነትና ክብሩ የሚገለጠው ሥልጣን ከሚመነጭበት ከሰፊው ሕዝብ ሉዓላዊ መብትና ፍላጎት ጋር የተሳሰረ በመሆኑ ነው። ምርጫ ከሚሰጠው ኃላፊነት በላይ ለእያንዳንዱ ዜጋ የዕለት ተዕለት ሕይወት መሻሻልና ከሀገር ሁለንተናዊ ዕድገት ጋር የተቆራኘ መሆኑን ሕዝቡ በትክክል ተገንዝቧል። ሦስተኛው ምሰሶ፦ የምርጫው የፖሊሲ ሐሳቦችና አማራጮች ከፍታ የታየበት ነው። በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የክርክር መድረኮች ተፎካካሪ ፓርቲዎች ያነሷቸውን የፖሊሲ አማራጮች ሕዝቡ በጥንቃቄ አዳምጧል። እነዚህ ሐሳቦች ለሀገር ዕድገት፣ ለጠንካራ መንግሥትና ለሰከነ የፖለቲካ ባህል ግንባታ መሠረት እንዲሆኑ በእያንዳንዱ ዜጋ ሕሊና ማስረፅ፣ በሰነድ በማዘጋጀትም መተግበር ይገባል። አራተኛው ምሰሶ፦ ምርጫ እንደ ማኅበራዊ ሀብት፤ ምርጫ ፖለቲካዊ ኩነት ብቻ ሳይሆን ትልቅ ማኅበራዊ ሀብት መሆኑን በተግባር አሳይቷል። ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ የዚህን ማኅበራዊ እሴት አንድምታ ሲያብራሩም "ሕዝባችን ስለ ኢትዮጵያዊ ቀናነቱና ፍቅሩ ጩኸቱን ሳይሆን የምርጫ ካርድ ድምፁን፣ ስላቅና ሃኬትን ሳይሆን ትሑትነቱን፣ የትኛውንም የፖለቲካ ሐሳብ ቢያራምድ እንኳን ማኅበራዊና ሀገራዊ ፍቅሩን ከጎኑ ላለው ወገኑ አለመንፈጉን ያየንበት እጅግ የተዋበ መድረክ ነበር። ስለዚህ የኢትዮጵያ ምርጫ ከፖለቲካዊ ፋይዳው ባልተናነሰ ሁኔታ ማኅበራዊ ፋይዳውም ከፍ ያለ ትልቅ የማኅበራዊ መሠረትን የሰጠው ነው።" ብለዋል። 8. የሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ታሪካዊ ሚና፦ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ስብራቶች የመፈወስ ዕድል ኢትዮጵያ በረጅም ዘመን የሀገረ መንግሥትና የፖለቲካ ሥርዓት ጉዞዋ ውስጥ በርካታ አኩሪ ታሪኮችን ብታስመዘግብም፣ በሂደቱ ውስጥ የተፈጠሩና ዛሬም ድረስ ሀገራዊ አንድነቷን፣ ሰላሟንና የዴሞክራሲ ግንባታዋን እየተፈታተኑ ያሉ ሥር የሰደዱ የፖለቲካ ስብራቶች መኖራቸው አይካድም። እነዚህን ለዘመናት የዘለቁ ስብራቶች በመጠገን ረገድ ይህ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሀገሪቱን ወደ አዲስ ምዕራፍ ሊያሻግር የሚችል ታሪካዊና ስትራቴጂካዊ ዕድል ይዞ መጥቷል። ምርጫው በበሰለና አካታች መንገድ በመመራቱ በሀገሪቱ የፖለቲካ ታሪክ ላይ ጉልህና አዎንታዊ አሻራ ማሳረፍ የሚችልባቸው ዋና ዋና አቅጣጫዎች አሉት። እነዚህም፦ የቅቡልነት ስብራትን ማከም፦ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የመንግሥታት ሥልጣን አመጣጥ አብዛኛውን ጊዜ ከኃይል ፖለቲካ ወይም ሙሉ በሙሉ ነፃ ካልሆኑ ምርጫዎች ጋር የተያያዘ በመሆኑ፣ የመንግሥት ሕዝባዊ ቅቡልነት ማጣት ለግጭቶች መነሻ ሲሆን ቆይቷል። ይህ ምርጫ ነፃና ታማኝ ሆኖ መካሄዱ አሸናፊው አካል ከሕዝብ የሚሰጠው እውነተኛ የሥልጣን አደራ እንዲኖረው ያደርጋል፤ ይህም በገዥው አካልና በሕዝቡ መካከል ያለውን መተማመን በማደስ ረገድ ትልቅ ዕድል ይሰጣል። የሰላማዊ ሥልጣን ሽግግር ባህልን መገንባት፦ ሥልጣንን በአፈሙዝ የመያዝ ልምድ ሀገሪቱን በተደጋጋሚ ለድቀት የዳረጋት መሆኑ ብዙ ትምህርት ሰጥቷል። በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሁሉም ወገኖች የሕዝብን ድምፅ አክብረው የሚቀበሉበት ድባብ መፈጠሩ ምርጫን ብቸኛ የሥልጣን መያዣና መልቀቂያ መንገድ የማድረግ አዲስና ጤናማ የፖለቲካ ባህል በሀገሪቷ ውስጥ እንዲለመድ ያደርጋል። በተቋማት ላይ ያለውን አመኔታ ማደስ፦ ሕዝቡ እንደ ምርጫ ቦርድ፣ ፍርድ ቤቶችና የዴሞክራሲ ተቋማት ባሉ ገለልተኛ መሆን በሚገባቸው ተቋማት ላይ ያለው እምነት መሸርሸሩ ሌላው ስብራት ሲሆን፣ ይህንንም ምርጫ በስኬትና በገለልተኝነት ማካሄድ መቻሉ የተቋማቱን ነፃነትና ብቃት በተግባር የሚያሳይ በመሆኑ ዜጎች በሀገሪቷ የሕግ የበላይነት ላይ ያላቸው እምነት መልሶ እንዲያገግም ያደርጋል። ብሔራዊ መግባባትን መፍጠር፦ አካታች የሆነ ምርጫ ማካሄድ መሣሪያ ያነሱ ወይም በሰላማዊ መንገድ የሚያምፁ የፖለቲካ ኃይሎች ቅሬታቸውን በሕዝብ ድምፅ እንዲፈትሹ በር ይከፍታል። ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የኢትዮጵያን የዘመናት የፖለቲካ ስብራቶች ለመፈወስ የራሱ አሻራ ሊያኖር የሚችለው ሂደቱ ፍትሐዊ፣ ግልጽና በርካታ የፖለቲካ ኃይሎችን ያሳተፈ፣ ከ54 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ በንቃት የተሳተፈበት በመሆኑ ነው። በዚህም ምርጫው በተሳካ ሁኔታ መካሄዱ በራሱ ወደ ሰፊው ብሔራዊ ምክክር ለመሻገር እንደ ትልቅ መነሻ ሆኖ ያገለግላል። ማጠቃለያ፦ ምርጫው ለአፍሪካ ዴሞክራሲ የብርሃን ፍኖት አፍሪካ በፖለቲካዊ አለመረጋጋቶች፣ በወታደራዊ ኃይሎች ጣልቃ ገብነትና ኢ-ሕገመንግሥታዊ መንገድ መምራት፣ የመንግሥት ግልበጣዎች እየተፈተነች ባለችበት በዚህ የታሪክ ምዕራፍ፣ ኢትዮጵያ በሰላማዊና ስልጡን መንገድ ምርጫዋን ማጠናቀቋ ለአህጉሪቱ አዲስ ፍኖተ ዴሞክራሲ ሆና እንድትወጣ አድርጓታል። 'የአፍሪካ ችግሮች የአፍሪካውያን መፍትሔዎች' የሚለውን መርህ በተግባር በማሳየት፣ የራሳችንን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት በራሳችን አቅም መቅረጽ እንደምንችል ለዓለም አሳይተናል። በዚህ አስቸጋሪ አህጉራዊ ድባብ ውስጥ፣ የፓን አፍሪካኒዝም ማዕከልና የአፍሪካ ኅብረት መቀመጫ የሆነችው ኢትዮጵያ ሰባተኛውን ጠቅላላ ምርጫ በሰላማዊና ፍትሐዊ መንገድ በስኬት ማጠናቀቋ ለአፍሪካ ትልቅ ተስፋን የሚሰጥ ነው። ኢትዮጵያ ለጫናዎች ሳትበገር፣ በራሷ ሁለንተናዊ አቅም ያከናወነችው ይህ ታሪካዊ መድረክ ሀገር በቀል ዴሞክራሲን እና አህጉራዊ ሉዓላዊነትን ያረጋገጠ በመሆኑ ለመላው አፍሪካ ኩራትና ተምሳሌት ሆኗል። የአፍሪካ ኅብረት የፖለቲካ ጉዳዮች፣ የሰላምና ደኅንነት ኮሚሽነር አምባሳደር ባንኮሌ አዶዬ፤ አህጉሪቱ ካለችበት ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር ዲሞክራሲ አማራጭ የሌለው መንገድ መሆኑን ገልጸው፤ ሰላምና ልማት ሊመጡ የሚችሉት በጠመንጃ ኃይል ሳይሆን ሕዝብ በነፃነት የራሱን መሪ በሚመርጥበት ስልጡን መንገድ ብቻ መሆኑን ተናግረዋል። ኮሚሽነሩ አክለውም፦ "አህጉራችን ከዲሞክራሲ ውጭ ሌላ ምርጫ የላትም። ወደፊት ለመራመድ፣ ዕድገትን ለማረጋገጥና በተለይም ዘላቂ ሰላምን ለመገንባት ከሁሉ የተሻለው መንገድ ዴሞክራሲ ብቻ ነው" ሲሉ በአፅንኦት ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ፣ ኢትዮጵያ ተቋማዊ አቅሟንና ሕጋዊ መሠረቷን በማጠናከር ወደ ተሻለ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ የተሻገረችበት እና የጋራ የትብብር አቅምን ያሳየችበት አዲስ ታሪካዊ ምዕራፍ ሆኖ በስኬት ተጠናቋል። ለዚህም ስኬት በየሚናቸው አስተዋጽኦ ላበረከቱ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ዕጩዎች፣ ሲቪል ማኅበራት፣ የጸጥታ ኃይሎች፣ የአፍሪካ ኅብረትና የኢጋድ ታዛቢ ቡድኖች፣ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች እንዲሁም ሀገር በቀል ታዛቢ ድርጅቶች በሙሉ ከፍ ያለ ምስጋና ይገባቸዋል። በምርጫው ወቅት የተሰጠው የሕዝብ አመኔታና ድምፅ ለተመራጮች ትልቅ አደራና ኃላፊነትን ጥሏል። ያሸነፉ ፓርቲዎችና ዕጩዎች ይህንን ታሪካዊ አደራ በመሸከም ለሕዝብ ፍላጎት ቅርብ የሆነ አገልግሎት በመስጠት፣ በታማኝነት፣ በቅንነትና ንጹሕ በሆነ ሕሊና በመሥራት የሕዝቡን ተስፋ ወደ ተጨባጭ ውጤት የመቀየር ግዴታ አለባቸው። የምርጫው ትልቁና የመጨረሻው ስኬት የሚለካው በተመራጮችና በሕዝብ መካከል በሚገነባው መተማመን፣ በሚረጋገጠው ዘላቂ ሰላምና ለሁሉም ተጠቃሚነትን በሚያሰፍነው ሀገራዊ ዕድገትና ብልጽግና ብቻ ነው።
የኢትዮጵያ ልዕልና በአረንጓዴው ከፍታ
Jun 25, 2026 2002
(በዮርዳኖስ ዓባይነህ) የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከልና የተራቆቱ መሬቶችን መልሶ ለማልማት የጀመረችው ታሪካዊና አርአያነት ያለው ብሔራዊ ንቅናቄ ነው። ይህ ዘመቻ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ሕፃናት፣ ወጣቶች፣ አዋቂዎችና ልዩ ልዩ ተቋማት በነቂስ በመውጣት በየዓመቱ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በከፍተኛ የሕዝብ ንቅናቄና በአንድነት መንፈስ ለመትከል ችለዋል። በዚህ ተከታታይ የችግኝ ተከላና እንክብካቤ ሥራ ምክንያት ለዓመታት ተራቁተው የነበሩ ተራራማና ኮረብታማ ቦታዎች እንዲሁም የሀገሪቱ የደን ሽፋን በከፍተኛ ሁኔታ እንዲያገግም ሆኗል፤ ይህም የአፈር መሸርሸርን ከመከላከል ባለፈ የከርሰ-ምድር ውሃ መጠን እንዲጨምር ተጨባጭ አስተዋጽኦ አበርክቷል። አካባቢን ከመጠበቅ ባሻገር፣ መርሃ-ግብሩ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን የፍራፍሬ፣ የቡናና የቅመማ ቅመም ችግኞችን በማካተት አርሶ አደሩ ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኝና የምግብ ዋስትናው እንዲረጋገጥ ትልቅ የኢኮኖሚ በር ከፍቷል። በተጨማሪም በዋና ዋና ከተሞች የተገነቡት ውብ አረንጓዴ ፓርኮች ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ፣ ንጹህና ማራኪ ከማድረጋቸውም በላይ ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ እየሆኑ ይገኛሉ። በአጠቃላይ የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ ለአሁኑ ትውልድ የኢኮኖሚ ዋስትናን፣ ለወደፊቱ ደግሞ የተስተካከለ የአየር ንብረትና ለምለም ሀገርን የሚያስረክብ ታላቅ የትውልድ ቅርስ በመሆኑ፣ የተተከሉትን ችግኞች ተንከባክቦ ማሳደግና ዘላቂነታቸውን ማረጋገጥ የሁላችንም የጋራ ኃላፊነት ነው። 👉ከተፈጥሮ ጋር የተጻረረው የሰው ልጅ ስልጣኔ የሰው ልጅ በምድር ላይ መኖር ከጀመረበት ጥንታዊ ዘመን አንስቶ በሕይወት ለመቀጠልና ሕልውናውን ለማረጋገጥ ከተፈጥሮ ብሎም ከመሰሎቹ ጋር ጠንካራ እና ቀጣይነት ያለው መስተጋብር ሲያደርግ ቆይቷል። ነገር ግን ይህ መስተጋብር ሚዛኑን እየሳተ መጥቶ፣ ከጥንቱ የግብርና ስልጣኔ እስከ ዛሬው የኢንዱስትሪ መስፋፋት ድረስ በሰው ልጅ እጅ የተፈጸመው የተፈጥሮ መራቆት በምድር ላይ ከባድ ጠባሳ ጥሏል። የደን መጨፍጨፍ፣ የአፈር መሸርሸር እና የውሃ አካላት መናመን የዚሁ አውዳሚ ጉዞ ውጤቶች ናቸው። አግባብ ያለው የአካባቢ ጥበቃ ባለመደረጉም፣ በቢሊዮን የሚቆጠሩ አዕዋፋትና የዱር እንስሳት ለዘመናት ከኖሩበትና ለነሱ ከሚስማማቸው ቀያቸው ለመሰደድ ተገድደዋል። የተባበሩት መንግስታት የምግብ እና ግብርና ድርጅት (FAO) በ2016 እ.ኤ.አ ባወጣው ጥናት መሠረት፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ በየዓመቱ 92 ሺህ ሄክታር ደን ይጨፈጨፋል። ለዚህም የእርሻ መሬት ማስፋፋትና የማገዶ ፍላጎት መጨመር በዋና ምክንያትነት ይጠቀሳሉ። ይህ የዓለም አቀፍ ስጋት ለሀገራችን ለኢትዮጵያ ደግሞ የራቀ ሳይሆን የውስጥ ቁስል ነበር። በደን መጨፍጨፍና በአፈር መሸርሸር ምክንያት በተደጋጋሚ የተከሰቱት የድርቅ፣ የረሃብ፣ የመሬት መንሸራተት እና የሕዝቦች መፈናቀል ታሪኮች የቅርብ ጊዜ ትዝታዎቻችን ናቸው። 👉የ"ክፉ ቀን" ትርክት እና የስነ-ልቦና ጠባሳ ከ1888 እስከ 1892 እ.ኤ.አ በሀገራችን የተከሰተውና '’ክፉ ቀን'’ ተብሎ የሚታወቀው አሰቃቂ የረሃብ ታሪክ ፣ ከዚያም በኋላ በወሎና በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የታዩት ድርቆች በዓለም መገናኛ ብዙሃን ጎልተው ሲዘገቡ ቆይተዋል። ይህ አሳዛኝ ክስተት ለውጭ መገናኛ ብዙሃንና ተቋማት ተጨማሪ ዝና እና ገቢ ማግኛ ሰበብ ሲሆን፣ ለሕዝባችን ግን ለዘመናት ያልተሻረ የስነ-ልቦና ቁስል ጥሎ አልፏል። ኢትዮጵያን በዓለም መድረክ የድህነት እና የረሃብ ተምሳሌት አድርጎ በመሳል፣ ኢትዮጵያውያንን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያንን አንገት ያስደፋ ጥቁር ታሪክ ሆኖ ኖሯል። ታዲያ ይህንን የውርደት ትርክት የሚቀይር፣ ሀገራዊ ክብርን የሚመልስና ቀጣይነት ያለው የአካባቢ ጥበቃን የሚያረጋግጥ ወሳኝ እርምጃ መውሰድ የህልውና ጉዳይ ነበር። 👉አረንጓዴ አሻራ፦ ተግዳሮቶችን የመለወጥ የፅናት ጉዞ በ2011 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት፣ በተቋማት ቅንጅትና በተደራጀ የሕዝብ ንቅናቄ "የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር" ተጀመረ። በመጀመሪያው ዓመት “40 ዛፎች በነፍስ ወከፍ” በሚል መሪ ሃሳብ የተጀመረው ዘመቻ፣ ከዕቅድ በላይ 18 በመቶ ስኬት በማስመዝገብ የሕዝቡን የልማት ጥም አሳየ። በሁለተኛው ዓመት (2012 ዓ.ም) ዓለምን ያሸበረው የኮሮና ቫይረስ (COVID-19) ወረርሽኝ ቢከሰትና ማኅበራዊ መራራቅ፣ ጥንቃቄዎች እንዲሁም ከቤት ሆኖ መሥራት ግዴታ ቢሆንም፣ የኢትዮጵያውያን የአረንጓዴ ጉዞ አልተገታም። “እየተጠነቀቅን እንተክላለን” በሚል መሪ ሐሳብ ፣ ማኅበረሰቡ ደህንነቱን ጠብቆ በመንቀሳቀሱ ከዕቅድ በላይ 14 በመቶ ችግኝ መትከል ተችሏል። 👉የሰባት ዓመታት ስኬቶች በቁጥር እና የስነ-ምህዳር መነቃቃት ይህ ስራ ለአንድና ለሁለት ዓመት የተደረገ ዘመቻ ሳይሆን የሰባት ዓመታት ተከታታይ የፅናት ጉዞ ነበር። ከ2011 እስከ 2017 ዓ.ም ባሉት ዓመታት ውስጥ በአጠቃላይ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች በኢትዮጵያ ምድር ላይ ተተክለዋል። የችግኞቹ የስብጥር ይዘትም ስልታዊ የደን ልማትን ያሳያል፦ 60 በመቶ የጥምር እርሻ ደን (Agroforestry) 35 በመቶ የተፈጥሮ ደን ሽፋን 5 በመቶ የከተማ ውበት ዛፎች ከተከናወኑት የክትትልና ቁጥጥር ሪፖርቶች መረዳት እንደሚቻለው፣ ከተተከሉት ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ውስጥ በአማካይ ከ75 በመቶ እስከ 80 በመቶ በላይ የመፅደቅ መጠን (Survival Rate) ማሳየት መቻላቸው የሥራውን ውጤታማነት በተጨባጭ ያረጋግጣል። ይህ መጠነ-ሰፊ ስራ ቀደም ሲል ከ2010 እስከ 2016 ዓ.ም ይከሰት የነበረውን የደን መጨፍጨፍ በ65 ሺህ ሄክታር በመቀነስ፣ የሀገሪቱን የደን ሽፋን በ11 ነጥብ 4 በመቶ ከፍ እንዲል አድርጓል። የተከናወነው የተቀናጀ የልማት ስራ የአፈር መሸርሸርን በመቀነስና የውሃ አካላትን በማንሰራራት ረገድ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። ይህ የደን ሽፋን ዕድገት ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከካርቦን ሽያጭ (Carbon Trading) እና ከአየር ንብረት አረንጓዴ ፋይናንስ (Green Finance) ልታገኝ የምትችለውን የኢኮኖሚ ዕድል በከፍተኛ ደረጃ የሚያሰፋላት ነው። 👉ከስነ-ምህዳር ጥበቃ ወደ ቢሊዮን ዶላር ኢኮኖሚ ግንባታ እና የኮሪደር ልማት የአረንጓዴ አሻራ ስኬት ስነ-ምህዳሩን በማደስ ብቻ አልተገደበም፤ የሀገሪቱን የኢኮኖሚ የጀርባ አጥንትም ጭምር ቀይሯል። መሬትን የማከምና የአፈር እርጥበትን የመመለስ ስራው በ2017 ዓ.ም 280 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ በሀገር ውስጥ ለማምረት አስችሏል። ይህ ውጤት ኢትዮጵያ ቀደም ሲል ለስንዴ ማስመጫ ታወጣ የነበረውን አንድ ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ያስቻለ ታሪካዊ ምዕራፍ ነው። በተጨማሪም ይህ አረንጓዴ ልማት ኢትዮጵያን በአፍሪካ 2ኛዋ የአቮካዶ ምርት ላኪ ሀገር ያደረጋት ሲሆን፣ በ2017 ዓ.ም የቡና ምርትን በማስፋፋትና ጥራትን በመጨመር 2 ነጥብ 6 ቢሊዮን ዶላር ታሪካዊ የውጭ ምንዛሪ ለማስመዝገብ አስችሏል። ይህ ታላቅ ስኬት የተገኘው የኢኮ-ሲስተም ልማትን፣ የገጠር ልማትን፣ የወንዝ ዳርቻ ልማትን እና የከተማ ኮሪደር ልማትን (Urban Corridor Integration) ባካተተ የተቀናጀ ስትራቴጂ ነው። በተለይም በአዲስ አበባና በተለያዩ ከተሞች የተከናወኑት የኮሪደር ልማት ስራዎች የከተማዋን ገጽታ በከፍተኛ ደረጃ ከመቀየር ባለፈ፣ ለነዋሪዎች ምቹና ሰፊ የእግር መንገዶችን፣ ማራኪ የአረንጓዴ ስፍራዎችንና መናፈሻዎችን በመፍጠር ለሀገር ውስጥና ለውጭ ሀገር ጎብኚዎች ደህንነቱ የተጠበቀና ማራኪ የከተማ ቱሪዝም (Eco-tourism) መዳረሻዎችን በተግባር መፍጠር ችሏል። 👉የአረንጓዴ ዲፕሎማሲ መሪነት እና ዓለም አቀፍ እውቅና ይህ ንቅናቄ በሀገር ውስጥ ካለው ፋይዳ ባለፈ፣ ኢትዮጵያ በአህጉራዊና በዓለም አቀፍ ደረጃ "የአረንጓዴ ዲፕሎማሲ" መሪ እንድትሆን አድርጓታል። እንደ ኤርትራ፣ ጅቡቲ፣ ፓኪስታን፣ ደቡብ ሱዳን እና ሩዋንዳ ያሉ ሀገራት ከኢትዮጵያ ተሞክሮ በመቅሰም በሀገራቸው የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር መጀመራቸው የዚህ ማሳያ ነው። በተጨማሪም የዓለም ምግብና ግብርና ድርጅት (FAO) ለጠቅላይ ሚኒስትሩ የ"አግሪፎድ ሻምፒዮን" እና "የላቀ የአፍሪካ አመራር ሽልማት" መስጠቱ ፣ ኢትዮጵያ 2ኛውን የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ምግብ ጉባኤን ማስተናገዷ እና በ80ኛው የፋኦ ጉባኤ ላይ ለሀገሪቱ አጠቃላይ ዕድገት የተሰጠው እውቅና የዓለምን አድናቆት ያረጋገጡ ክስተቶች ናቸው። እነዚህ ዓለም አቀፍ ምስክርነቶች ኢትዮጵያ ቀደም ሲል ተስሎባት የነበረውን የድርቅ እና የረሃብ አፍራሽ ትርክት በአረንጓዴ ልማት፣ በአንድነት እና በምርታማነት በተግባር የቀለበሰችበት ታላቅ ድል ነው። 👉ስምንተኛው ዙር የአረንጓዴ ዐሻራ፡ "ተስፋን እንትከል!" ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቢሾፍቱ ሆራ አርሰዲ ሐይቅ የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ማስጀመራቸው ይታወቃል። መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ብልፅግና አሰናስሎ የሚያረጋግጥ ብሔራዊ የልማት አቅጣጫ መሆኑ ተመስክሮለታል። የዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ ዘመቻ "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሐሳብ መጀመሩ ጥልቅ ትርጉም አለው። ተስፋ የነገን ብሩህ ምዕራፍ ዛሬ ላይ ለመጻፍ የሚያስችል አረንጓዴ መቀነት ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉትም፤ አረንጓዴ ዐሻራ አፈራችንን ከስደት፣ የታላቁን ህዳሴ ግድባችንን ደግሞ ከደለል የሚታደግ ብሔራዊ ጋሻ ሆኗል። የአባቶቻችን የዓድዋ ድል ወራሪን ያሳፈረ ታላቅ ገድል እንደነበረ ሁሉ፣ የአሁኑ ትውልድ በአረንጓዴ ዐሻራ እያከናወነ ያለው ተግባርም ለቀጣዩ ትውልድ የሚሻገር አዲስ የታሪክ ገድል እየሆነ ይገኛል። ይህ ንቅናቄ የሀገሪቱን የተረጂነት ታሪክ ወደ ማድረግና ራስን ወደ መቻል ዘመን የሚያሸጋግር የመደመር መርህ መገለጫ ነው። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ ጉዞ ቁጥራዊ መረጃዎች የህዝብ ቁርጠኝነት ማሳያ ናቸው። ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ከ48 ቢሊየን በላይ ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያላቸው ችግኞች ተተክለዋል። በዘንድሮው መርሃ ግብር ደግሞ ከ8 ቢሊየን በላይ ችግኞችን ለመትከል የታቀደ ሲሆን፤ ይህም አጠቃላይ የተተከሉትን ችግኞች ቁጥር ወደ 56 ቢሊየን ያደርሰዋል። ይህ ታላቅ ስኬት እዚህ ላይ አያበቃም፤ ሀገሪቱ በፈረንጆቹ 2029 የሚካሄደውን የዓለም አቀፉን የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (COP32) ስታስተናግድ፣ በአጠቃላይ 65 ቢሊየን ችግኞችን መትከል የቻለች መሪ ሀገር መሆኗን ለዓለም የምታበስርበት ታሪካዊ ምዕራፍ ይሆናል። በክረምቱ ወራት እያንዳንዱ ዜጋ "ተስፋን በመትከል" የዓድዋን የኩራት ስሜት በአረንጓዴ ልማት ሊደግመው ይገባል። የበለፀገችና የተከበረች ኢትዮጵያን ለቀጣዩ ትውልድ ለማስረከብ፣ የተተከሉትን ችግኞች ተንከባክቦ ማሳደግና የአረንጓዴ ዐሻራን ስኬት ማስፋትና ማስቀጠል የዛሬው ትውልድ የማይታጠፍ ብሔራዊ ጥሪ ነው። 👉የወደፊት ስትራቴጂካዊ አቅጣጫዎች በኢትዮጵያ እስከአሁን የተመዘገቡ ስኬቶችን ዘላቂ ለማድረግና የተፈጥሮ ቅርሶቻችንን ይበልጥ ለማጠናከር የወደፊት የትኩረት አቅጣጫዎች በግልጽ ተቀምጠዋል። መንግሥት የልማቱን የሕዝብ ባለቤትነት ማረጋገጥና ማቀናጀት፣ አረንጓዴ ልማትን እንደ ባህል መገንባት፣ የቴክኖሎጂ እሴቶችን በመጠቀም የሥራ ዕድሎችን ማስፋፋት፣ በተፈጥሮ ሀብት ላይ የሚደረገውን ጫና መቀነስ፣ እንዲሁም አዲስ የተገነቡ የኮሪደር ልማቶችንና ፓርኮችን በመጠበቅ የጎብኝዎችን ደህንነት ማረጋገጥና የተፈጥሮ ቅርስን አብሮ ማጠናከር ላይ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባ አቅጣጫ አስቀምጧል።
የሀዋሳ ቀጣይ የዕድገትና የውበት ምዕራፍ
Jun 24, 2026 688
ሀዋሳ፤ ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፦የሀዋሳ ቀጣይ የዕድገትና የውበት ምዕራፍ በእንዳለ ደበላ (ሀዋሳ ኢዜአ) ‎ታቦር ተራራን በአንድ ጎኗ አላሙራ ተራራን ደግሞ በሌላው ጎኗ ታቅፋ የከተመችው ሀዋሳ ከተማ የፍቅር ሐይቅን ጨምሮ የተለያዩ የመስህብ ስፍራዎችንም በጉያዋ አቅፋ ይዛለች። ለባህላዊ ሕክምና አገልግሎት ጭምር የሚውሉት የወንዶገነት እና የይርጋለም የተፈጥሮ ፍል ውሀዎች ከሀዋሳ በቅርብ ርቀት ላይ መገኘታቸው ከተማዋ የቱሪስት መዳረሻ እንድትሆን በማድረግ በኩል የራሳቸው አስተዋጽኦ አላቸው። የሲዳማ ክልል ርዕሰ መዲናዋ ሀዋሳ ካሏት ተፈጥሯዊ የመስህብ ስፍራዎች በተጨማሪ የተለያዩ ባህላዊና ሀይማኖታዊ በዓላት በድምቀት የሚከበሩባት መሆኑም በጎብኚዎች ተመራጭ አድርጓታል። ሀዋሳ ባላት የተፈጥሮ ሀብት ላይ ተጨማሪ ውበትን ያላበሳት የኮሪደር ልማትም ከተማዋን ለኑሮ፣ ለሥራና ለኢንቨስትመንት ይበልጥ ምቹና ተመራጭ እያደረጋት ነው።   ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደከተማዋ የሚመጡ ጎብኚዎች ቁጥር እንዲበራከትና የቆይታ ጊዜያቸውንም እንዲያራዝሙ በማድረግ በኩል የኮሪደር ልማቱ አዎንታዊ ሚና መጫወት ጀምሯል። በከተማዋ ከሪፈራል ሰርክል እስከ መንቦ፣ ከሳውዝ ስፕሪንግ እስከ ፍቅር ሐይቅ፣ ከፍቅር ሐይቅ እስከ ሳውዝ ስታር ሆቴል የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች በተፈጥሮ የታደለችውን ሀዋሳን የበለጠ አድምቋታል። ውበቷን አጉልቶ ከማውጣት በተጨማሪ የከተማዋ ገቢ በማሳደግ በኩልም ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ነው። የሲዳማ ክልል ገቢዎች ባለስልጣን ምክትል ሀላፊና የደንበኞች አገልግሎት የታክሰ አሰባሰብ ዘርፍ ሀላፊ ወይዘሮ ሙላት ዮሴፍ በእዚህ ሀሳብ ይስማማሉ። እሳቸው እንዳሉት ባለፉት 11 ወራት በከተማዋ 6 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰብ ተችሏል።   አምና በተመሳሳይ ወቅት 5 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ገቢ እንደተሰበሰበ አስታውሰው የዘንድሮው 1 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ብልጫ አለው ብለዋል። ለገቢው መጨመር በምክንያትነት ከጠቀሷቸው አንዱ የኮሪደር ልማቱን ተከትሎ የንግድ እንቅስቃሴውና የጎብኚው ቁጥር እያደገ መምጣት ነው። ይህን የከተማዋን የገቢ አቅም የበለጠ ለማሳደግ ያስችላል የተባለለት ተጨማሪ የኮሪደር ልማትም በአሁኑ ወቅት ሥራው ተጀምሯል። ከሳውዝ ስታር ሆቴል በቀድሞው መናኸሪያ እስከ ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የተጀመረው የኮሪደር ልማት ሥራ አንዱ ሲሆን በፍጥነት ለማጠናቀቅም ታቅዶ እየተሰራ ነው። ሀዋሳ የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከልነቷልን ይበልጥ ለማሳደግ አሁንም በትጋት እየሰራች ነው፤ አሁንም ልማት ላይ ነች። ከከተማዋ መግቢያ የሐይቅ ዳርቻ ጀምሮ እስከ ታቦር ተራራ ድረስ 12 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የሐይቅ ዳርቻ ልማት ተጀምሯል። ይህም የከተማዋን እድገት ከማስቀጠል ባለፈ ይበልጥ የሚያደምቃት ነው። ተመራጭነቷነም ከፍ ያደርገዋል። በስድስት ወራት ውስጥ እንዲጠናቀቅ ታቅዶ ወደሥራ የተገባው የሐይቅ ዳርቻ የኮሪደር ልማት በመጀመሪያ ምዕራፍ ሥራ የፍቅር ሐይቅ መግቢያ፣ አሞራ ገደል እና አሣ ገበያ አካባቢዎችን አካቶ የሚገነባ ነው። የሐይቅ ዳርቻ ልማቱ 60 ሜትር ወደ ሐይቁ ተገብቶ የሚከናወን ሲሆን ሰው ሰራሽ የውሀ ፏፏቴ፣ በሐይቁ ዳርቻ የእግረኛና የብስክሌት መንገድ፣ የተለያዩ ሱቆች፣ ሬስቶራንት፣ የመመልከቻ ማማዎች እንዲሁም ሌሎች መዝናኛዎችን አካቶ የሚሰራ ነው። ልማቱ ተጠናቆ ወደአገልግሎት ሲገባ በከተማዋ የቱሪዝም እንቅስቃሴ ላይ አዎንታዊ አበርክቶ ይኖረዋል።   ‎የከተማዋ የቱሪዝም መረጃ እንደሚያሳየው ካለፉት ዓመታት ወዲህ በሀዋሳ ከተማ የቱሪስት ፍሰት እየጨመረ መጥቷል። በተለይ በኮንፈረንስ ቱሪዝም ረገድ እና በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት በኩል እየታየ ያለው ለውጥ ከተማዋን በቱሪስቶች ይበልጥ ተመራጭ አድርጓታል። ‎ሀዋሳ ከተማ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግን ጨምሮ የተለያዩ ስፖርታዊ ውድድሮችን ለማስተናገድ ተመራጭ መሆኗ በስፖርት ቱሪዝም ዘርፍ ይበልጥ እንድትታወቅ እያደረገ ነው። ክለባቸውን ለመደገፍ ወደከተማዋ የሚመጡ ደጋፊዎች ዘርፉ እንዲነቃቃ የራሳቸውን አሻራም እያሳረፉ ይገኛሉ። በሀዋሳ ከተማ የሚከበሩ ሀይማኖታዊና ባህላዊ በዓላትም ከተማዋ በርካታ እንግዶችን እንድታስተናግድ ከማድረጋቸው ባለፈ ለከተማዋ ገቢ መጨመር የራሳቸውን አስተዋጽኦ አበርክተዋል። የዓለም ቅርስ ሆኖ የተመዘገበው የሲዳማ ዘመን መለወጫ በዓል (ፊቼ ጨምበላላ) ለእዚህ ጥሩ ምሳሌ ነው። የጎብኚዎችን ቀልብ የሚስበው ይሄ በዓል ሌላው የሀዋሳ ከተማ ድምቀት ነው። በየዓመቱ በፍቼ ጨምባላላ በዓል ላይ ለመታደም ከሀገር ውስጥና ከመላው ዓለም በርካቶች ወደሀዋሳ ከተማ ስለሚመጡ ዋነኛው የቱሪስት መስህብ ነው ማለት ይቻላል። እነዚህ ባህላዊ፣ ሀይማኖታዊና ተፈጥሯዊ እሴቶችን በአግባቡ በማልማትና በማጎልበት ሀዋሳን ይበልጥ የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በቅርቡ የግንባታ ሥራው የተጀመረው የሀዋሳ ፍቅር ሐይቅ ዳርቻ ልማት ለእዚህ አንድ ማሳያ ነው። ልማቱ ከተማዋን የሀገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ ብሎም የዓለም ኮንፈረንስ ማዕከል ለማድረግ ትልቅ ራዕይ ይዞ የተጀመረ ነው። ይህን የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ የኮሪደር ልማት በይፋ ያስጀመሩት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ናቸው። የፍቅርና የሕብር ተምሳሌት የሆነችውን ሀዋሳ ውበቷን ይበልጥ ለማውጣትና ተመራጭ ለማድረግ የክልሉ መንግስት አበክሮ ይሰራል ነው ያሉት።   እንደእሳቸው ገለጻ የኮሪደር ልማት ሥራው በፍጥነት እየተከናወነ የሚገኝ ሲሆን በቀጣይም ከሀዋሳ ሐይቅ እስከ ሞኖፖል ድረስ ያለውን አካባቢ በአምስተኛ ዙር የኮሪደር ልማት ለማልማት ታቅዷል። ሀዋሳን የኮንፈረንስ፣ የስፖርትና የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ ትልቅ ዕድል ይዞ ለሚመጣው የሀዋሳ ሀይቅ ዳርቻ ልማት የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ተናግረዋል። የሀዋሳ ከተማን በሀገር ውስጥና በአፍሪካ ተመራጭ የኮንፈረንስ ማዕከል ለማድረግ እንደሚሰራ የገለጹት ደግሞ የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጥራቱ በየነ ናቸው።   ከተማዋን ይበለጥ ተመራጭ ለማድረግ ለሚከናወነው የመጀመሪያ ዙር የሐይቅ ዳርቻ ልማት 3 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ያስፈልጋል። ከዚህ ውስጥ ደግሞ 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን የሚሆው ከማህበረሰቡ የሚሰበሰብ መሆኑን ነው ከንቲባው የገለጹት። ህዝቡም የከተማዋን ልማት ለመደገፍ የአቅሙን እያገዘ ነው። ለልማቱ በአይነት፣ በገንዘብና በዕውቀት እያደረገ ያለው ድጋፍ በቀጣይም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አንስተዋል። የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ከ1 ሺህ ለሚበልጡ ሰዎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጠር ያነሱት ደግሞ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሀዋሳ ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ሀላፊ አቶ ቸርነት ፍላቴ ናቸው። በሀዋሳ በተለያዩ ምዕራፎች የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች እስካሁን ከ2ሺህ ለሚበልጡ ሰዎቸ የሥራ ዕድል በመፍጠር ለበርካቶች ተጨማሪ ጥቅምን አስገኝቷል። የልማት ሥራዎች ለከተማዋ ነዋሪዎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ሀዋሳን ውብ፣ ምቹና ለኑሮ ተመራጭ ከተማ እያደረጓት በመሆኑ በቀጣይም ህብረተሰቡን በማሳተፍ ልማቱ እንደሚጠናከር ነው የገለጹት። ‎‎ከታቦርና አላሙራ ተራሮች እግር ሥር የከተመችው ሀዋሳ ዛሬም በሥራ ላይ ናት፣ የሚሰሩ ልጇቿ ዛሬም ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ ከተማዋን ይብልጥ ከፍ ለማድረግ እየታተሩ ነው። የከተማዋን የቀጣይ የዕድገትና የውበት ምዕራፏን እውን ለማድረግ ልጆቿ በአቅማቸው አሻራቸውን ለማሳረፍ ወደተግባራዊ ሥራ ገብተዋል። በማማዋ ላይ ከፍ ብላ ጎልታ እንድትታይ የሚያደርጉት ርብርብ በዚህ ከቀጠለ ራዕዩዋን በማሳካት ሀዋሳን ከሀገር ውስጥ ባለፈ የአፍሪካ ኮንፈረንስ ማዕከል የማድረግ ግብ መሳካቱ አይቀሬ ነው።
የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኮኖሚያዊ ትሩፋት
Jun 23, 2026 1267
በዮሐንስ ደርበው ከሰብል ልማት አኳያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጭነት በ2011 ዓ.ም ጅማሮውን ያደረገው የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ አሁን ዘርፈ-ብዙ ጥቅሙ በተጨባጭ እየተገለጠ ነው። ከበርካታ ትሩፋቶቹ መካከልም የምርታማነት ማደግ ተጠቃሽ ነው።ይህን ተከትሎም የሕብረተሰቡ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት አድጓል። ይህን ሐሳብ በአኃዝ አስደግፎ ለማየት ያህል፤ ከአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ በፊት (በ2010 ዓ.ም) በሔክታር የሚመረተው ስንዴ 22 ኩንታል፣በቆሎ 30 ኩንታል፣ ጤፍ 17 ኩንታል እንዲሁም ገብስ 23 ኩንታል ነበር። ከኢንሼቲቩ ትግበራ በኋላ ደግሞ (በ2017 ዓ.ም) ስንዴ በሔክታር 36 ኩንታል፣ በቆሎ 46 ኩንታል፣ ጤፍ 20 ኩንታል፣ ገብስ 30 ኩንታል ማምረት ተችሏል። በዚህም መሠረት በ2017 ዓ.ም 7 ነጥብ 8 ሚሊየን ሔክታር መሬት በስንዴ ሰብል በመሸፈን 280 ሚሊየን ኩንታል ማምረት ተችሏል። ስንዴን በትጋት በማምረትም ከውጭ ለማስገባት ይወጣ የነበረን 1 ቢሊየን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማስቀረት ተችሏል። በአረንጓዴ ዐሻራ ጸንቶና ተግቶ መሥራት ዘመኑ የሚፈልገው ዐርበኝነት አረንጓዴ ዐሻራ - ለዓየር ንብረት ለውጥ ላለመበገር የሚደረግ ትጋት ከአፍሪካ ሰማይ እስከ ዓለም ከፍታ ከፍራፍሬ አኳያ የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ በፍራፍሬው ዘርፍ ዕድገትም ከፍተኛ አስተዋጽዖ አበርክቷል። በዚህም ገበያውን ከማረጋጋት ባለፈ ሕብረተሰቡ (አምራቹ) ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱ በዚያው ልክ እንዲያድግ አስችሏል።   ኢትዮጵያም በአፍሪካ አቮካዶን በቀዳሚነት ወደ ውጭ የምትልክ ሁለተኛዋ ሀገር እንድትሆን አስችሏታል። ከቡና ልማት መስፋፋት አኳያ ሌላኛው የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ በረከት የቡና ልማት መስፋፋትና የውጭ ምንዛሬ ማደግ ነው። ይህን በአሥረጂ አስደግፈን ብንመለከት፤ በ2011 ዓ.ም በ600 ሺህ ሔክታር ላይ ቡና ተተክሏል። 500 ሺህ ሜትሪክ ቶን የቡና ምርት ተሰብስቧል።738 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር ገቢ ተገኝቷል። እንዲሁም በ2017 ዓ.ም 1 ነጥብ 4 ሚሊየን ሔክታር መሬት ላይ ቡና ተተክሏል። 1 ነጥብ 58 ሚሊየን ሜትሪክ ቶን የቡና ምርት ተሰብስቧል። 2 ነጥብ 65 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር ገቢ ማግኘት ተችሏል። ከሥራ ዕድል ፈጠራ አኳያ ከአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ጋር በተያያዘ ለ2 ነጥብ 5 ሚሊየን ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል። ከላይ የተጠቀሱ ማሳያዎችን (ናሙናዎችን) ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ በቀጥታ ለሕዝቡ ጥቅም የቆመ መርሐ-ግብር መሆኑን መገንዘብ አያዳግትም። ስለዚህ በቀጣይ ሕብረተሰቡ በዚህ ኢኒሼቲቭ ላይ ያለጠባቂነት በንቃት በመሳተፍ እና ባሕሉ በማድረግ ተጠቃሚነቱንም በዚያው ልክ ለማሳደግ መትጋት ይጠበቅበታል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሐሳብ በቢሾፍቱ ማስጀመራቸው ይታወሳል። ባለፉት ዓመታት 48 ቢሊየን ችግኞች የተተከሉ ሲሆን፤ በዘንድሮው መርሐ-ግብር ደግሞ 8 ቢሊየን ችግኞችን ለመትከል ግብ ተቀምጧል። #አረንጓዴ_ዐሻራ #ኢዜአ #Ethiopian_News_Agency #ተስፋን_እንትከል
እንደዋዛ የበርካቶችን በር የሚያንኳኳው ዲጂታል (ቨርቹዋል) ኦቲዝም
Jun 5, 2026 13180
የጤና ነገር በዮሐንስ ደርበው እንደዋዛ የበርካቶችን በር የሚያንኳኳውን ዲጂታል (ቨርቹዋል) ኦቲዝም እንዴት መከላከል ይቻላል? አንድ ሰው ኦቲዝም አለበት የሚባለው ምን ዓይነት ምልክቶች ሲታዩበት ነው? ከቨርቹዋል ኦቲዝም መንስዔ፣ ምልክቶቹ፣ የሚያስከትለው ጉዳትና ሊደረጉ ስለሚገባቸው ጥንቃቄዎች የአዕምሮ ሕክምና ባለሙያ ወ/ሮ መዓዛ መንክር ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ አብራርተዋል። መነሻ ልጆች በአራት የዕድገት ዘርፎች እንደሚያድጉ ያነሱት ወ/ሮ መዓዛ፤ እነሱም የቋንቋ ክኅሎት ዕድገት፣ የአዕምሮ (ነገሮችን፣ ሁኔታዎችን) የመረዳት ዕድገት፣ አካላዊ ዕድገት እና የማኅበራዊ መሥተጋብርና የተግባቦት ዕድገት መሆናቸውን ያብራራሉ። በዚህም መሠረት ይላሉ ባለሙያዋ፤ አንድ ልጅ ጤናማ ወይም ሙሉ ዕድገት አለው የሚባለው በአራቱም የዕድገት ደረጃዎች በተመጣጠነ ሁኔታ ሲያድግ መሆኑን ነው ያስገነዘቡት። ምንድንነት? ባለሙያዋ ኦቲዝም በሁለት ተከፍሎ እንደሚታይ ጠቁመው፤ የመጀመሪያው ከመጀመሪያ ጀምሮ በሕክምና የተረጋገጠ በኦቲዝም ጥላ ሥር ያሉ ልጆች ወይም “ኦቲዝም ስፔክትረም ዲስኦርደር” (ዋናው ኦቲዝም) እንደሚባል ይገልጻሉ። ሁለተኛው ቨርቹዋል ኦቲዝም መሆኑን ገልጸው፤ ይህ ማለት ደግሞ ኦቲዝም የሚመስል ምልክቶች የሚያሳዩ ልጆችን የሚገልጽ እንጅ፤ ዋናው ኦቲዝም እንዳልሆነ ያስረዳሉ። ነገር ግን ይላሉ ወ/ሮ መዓዛ፤ አንድ ልጅ ከላይ ከተገለጹት ከአራቱ ሁለቱ በተለይም የቋንቋ ክኅሎት እና የማኅበራዊ መሥተጋብርና የተግባቦት ዕክል ሲገጥመው፤ ዋናው ኦቲዝም አለበት እንደሚባል አስገንዝበዋል። የጡት ካንሰርን ለመከላከል ለልብ ህመም አጋላጭ መንስዔዎች በወቅቱ ካልታከመ ለኩላሊት መድከም፣ ለደም መመረዝና ለሞት የሚያደርሰው በዓለም ላይ አሳሳቢ ደረጃ ከደረሱ የህመም ዓይነቶች አንዱ ለቨርቹዋል ኦቲዝም አጋላጭ ምክንያቶች ምንድን ናቸው? ልጆች ከተወለዱ እስከ 3 ዓመት ባለው ዕድሜያቸው ለተንቃቃሽ ስልኮች፣ ታብሌቶች፣ ቴሌቪዥን (ለስክሪኖች) ለረጅም ሠዓታት በድግግሞሽ ተጋላጭ ሲሆኑ ለኦቲዝም መሰል ምልክቶች (ቨርቹዋል ኢቲዝም) ተጋለጡ ተብሎ እንደሚወሰድ የአእምሮ ሕክምና ባለሙያዋ ተናግረዋል። ይህን ተከትሎም ልጆች ከሰዎች ጋር ባለመቀራረብ፣ በገሃዱ ዓለም የሚደረገውን ነገር ካላማየት የተነሳ ያልተለመዱ (አዳዲስ) ባሕርያትን እንደሚያዳብሩ ጠቁመው፤ እነዚህ ባሕርያትም ኦቲዝም መሰል (ቨርቹዋል ኦቲዝም) መሆናቸውን ይገልጻሉ። ጉዳዩን በምሳሌ ሲያብራሩም፤ ከዕድሜ እኩዮቻቸው ጋር ተግባብቶ መጫወት ምን እንደሆነ አለማወቅ፣ ተረጋግቶ መቀመጥ አለመቻል፣ በገሃዱ ዓለም ለሚደረጉ ነገሮች ትኩረት አለመስጠት፣ የእንቅልፍ መዛባት፣ ለስክሪን እና ዲጂታል ለሆኑ ነገሮች ሱሰኛ መሆን (ምግብ ሲበሉ ሞባይል መያዝ፣ ቴሌቪዥን ዕያዩ መብላት መፈለግ)፣ ማንኛውንም ነገር ሞባይል ወይም ቴሌቪዥን ካልተከፈተ ማድረግ አለመቻል (አለመፈለግ) የሚሉት የቨርቹዋል ኦቲዝም ምልክቶች መሆናቸውን ነው የዘረዘሩት። ይህን ተከትሎም ይላሉ ባለሙያዋ፤ የቋንቋ ክኅሎታቸው እንደ ዕድሜ እኩዮቻቸው የዳበረ አይሆንም፤ ከዚህም ሲያልፍ ኦቲዝም መሰል ምልክቶች በሚኖሩበት ወቅት በቀላሉ ከማኅበረሰቡ ጋር ለመግባባት በጣም ይቸገራሉ ሲሉ አስገንዝበዋል። የኦቲዝም መንስዔ ምንድን ነው? እንዴት መጣ? የሚለው እስካሁን በመጠናት ላይ መሆኑን የሚገልጹት ባለሙያዋ፤ ቨርቹዋል ኦቲዝም ግን መንስዔው እንደሚታወቅ አረጋግጠዋል። መንስዔውም ልጆች ለረጅም ሠዓትና በድግግሞሽ (ለብዙ ጊዜያት) ለስክሪን ተጋላጭ መሆናቸው ነው ይላሉ። ልጆች ቴክኖሎጂን መቼ ይጠቀሙ? እንደ ባለሙያዋ ገለጻ፤ ልጆች ከተወለዱ እስከ ሁለት ዓመት በፍጹም እንዳይጠቀሙ ይመከራል። በአንጻሩ ከወላጆቻቸው ጋር እንዲያወሩ፣ አካባቢያቸውን እንዲያዩ፣ በመንቀሳቀስና በመነካካት ገሃዱን ዓለም እንዲረዱ እንደሚመከር አመላክተዋል። ቴክኖሎጂን መጠቀም አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘ ከሁለት እስከ ስድስት ዓመታቸው፤ ቋንቋን (ንግግርን) የሚያበረታቱ፣ ትምህርት ሰጭ ሆነው ከተገኙ ከአዋቂዎች ጋር በመሆን የጨዋታ ክኅሎትን የሚያዳብሩ ንግግር ያላቸው (መዝሙሮችና ሌሎችንም) በቀን ለ30 ደቂቃ እንዲመለከቱ ማድረግ ይመከራል ብለዋል። ንግግር የሌላቸው ቪዲዮዎች ግን ልጆች ከፊልሙ ዐይተው እንኳን ቋንቋ እንዳይማሩ ስለሚገድቡ ለልጆች ተገቢ አይደሉም ይላሉ። ከሁለት እስከ ስድስት ዓመት ለሆናቸው ግን ትምህርታዊ ጉዳይ ከሆነ እና ልጄ ስነግረው ስላልገባው በስክሪን ሳሳው ሊገባው ይችላል ብለው ወላጆች ሲያስቡ ለዚያውም ከአዋቂዎች ጋር በመሆን ለማስተማር ብቻ እስከ 30 ደቂቃ በቀን መጠቀም ቢችሉ ጥሩ ነው ብለዋል። እነማን ተጋላጭ ናቸው? ብዙ ጊዜ ወላጆች ባለማወቅ ልጆች ሲንቀሳቀሱ፣ ያገኙትን ሲነካኩ ጥፋት ይከሰታል፣ ይወድቃሉ … በሚል እሳቤ አርፈው እንዲቀመጡ በማሰብ ስልክ ይሰጧቸዋል፤ ቴሌቪዥንም ይከፍቱላቸዋል የሚሉት ወ/ሮ መዓዛ፤ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ሉ ልጆች ተጋላች መሆናቸውን አንስተዋል። ስለዚህ ወላጆች ለረጂም ሠዓት እና በተደጋጋሚ ጊዜ ታብሌት፣ ስልክ እና ቴሌቪዥን ለልጆች መክፈት ለቨርቹዋል ኦቲዝም እንደሚያጋልጥ ተገንዝበው፤ የልጆቻቸውን ጤና ከማወክ ቢቆጠቡ መልካም መሆኑን አመላክተዋል። ልጆች በቨርቹዋል ኦቲዝም መጠቃታቸውን ማወቅ ይቻላል? እንደ ወ/ሮ መዓዛ ማብራሪያ፤ ልጆች በቨርቹዋል ኦቲዝም መያዛቸውን ወላጆችም በቤታቸው ማወቅ ይችላሉ፤ ወደ ሕክምና ተቋም በመሄድም በምርመራ ማወቅ ይቻላል። ወላጆች በቤት ውስጥ መለየት የሚችሉበት ስልትም፤ ቴሌቪዥን ሲጠፋ፣ ሞባይል ሲከለከሉ ልጆች በከፍተኛ ሁኔታ የሚበሳጩ ከሆነ፣ ምግብ አልበላም የሚሉ ከሆነ፤ አልታዘዘም ካሉ፣ ተረጋግተው የማይቀመጡ ከሆነ፣ እየተንቀሳቀሱ ቁጣቸውን የሚገልጹ ከሆነ እነዚህ ምልክቶች ሱስ እንደሆነባቸው ይጠቁማል ይላሉ። በተጨማሪም የንግግር መዘግየት ካለ፣በአካባቢያቸው ስለሚከናወኑ ሁኔታዎች ብዙም ትኩረት የማይሰጡ ከሆነ የቨርቹዋል ኦቲዝም ምልክቶች መሆናቸውን በመግለጽ፤ ለተሻለ የባለሙያ እገዛ በዚህ ጊዜ ልጆችን ወደ ሕክምና ተቋም መውሰድ እንደሚገባ ይመክራሉ። ሕክምና ቀዳሚው የሕክምና አካል የኦቲዝሙን ዓይነት በምርመራ መለየት መሆኑን ወ/ሮ መዓዛ አስረድተዋል።ይህም ማለት በኦቲዝም ጥላ ሥር ያሉ ልጆች (ኦቲዝም ስፔክትረም ዲስኦርደር) ነው ወይስ ቨርቹዋል ኦቲዝም ነው የሚለው ከተለየ በኋላ ወደ ቀጣዩ ሂደት መሄድ ይገባል ይላሉ። በዚህም መሠረት፤ ልጆ ከስክሪን (ቴሌቪዥን፣ ሞባይል፣ ታብሌት…) እንዲከለከሉ ማድረግ የሕክምናው አካል መሆኑን ነው ያመላከቱት። በተጨማሪም ከቤት ወጥተው ከልጆች ጋር እንዲጫወቱ ብሎም የገሃዱን ዓለም እንቅስቃሴ፣ የአኗኗር ሁኔታ እንዲያዩ እና እንዲረዱ ማድረግ ተገቢ ነው ብለዋል። የቋንቋ (ንግግር) መዘግየቱ ከባድ ከሆነ (ከእኩዮቻቸው በጣም ወደ ኋላ የቀሩ ከሆነ) ደግሞ ልጆቹ “ስፒች ቴራፒ” እንዲያገኙ ማድረግ እንደሚገባም መክረዋል። አክለውም ወላጆች ልጆችን ወደ ቤተሰብ እንዲሁም ወደ መዝናኛ ስፍራ ይዘዋቸው በመሄድ ከሰዎች ጋር ያላቸውን መቀራረብ እንዲያሳድጉ ትኩረትና ጊዜያቸውን ለልጆች መስጠት እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል። ወ/ሮ መዓዛ እንዳሉት፤ ከላይ የተጠቀሱት አማራጮች ተደርገው መሻሻል ከሌለ (ልጆቹ ካልተሻላቸው) ዋናው ኦቲዝም (በኦቲዝም ጥላ ሥር ያሉ ልጆች/ኦቲዝም ስፔክትረም ዲስኦርደር) ሊሆን ይችላል ብለዋል። ስለዚህ ለዚህኛው የሚሆነውን የሕክምና ክትትል በባለሙያ ታግዘው ማከናወን ይኖርባቸዋል ነው ያሉት። በአጠቃላይ ግን የኦቲዝም ሕክምና ባብዛኛው ከመድኃኒት ይልቅ በትምህርታዊ ሥልጠና በመታገዝ የሚሰጥ መሆኑን ገልጸው፤ የሚድንበትን ጊዜ ማወቅ እንደማቻል አመላክተዋል። በእርግጥ መድኃኒት የሚታዘዝበት ጊዜም እንዳለ ጠቁመው፤ ይህም ከፍተኛ የሆነ የእንቅልፍ ማጣት ካለ፣ ቤተሰብን የመረበሽ ነገር ካለ፣ ከፍተኛ የሆነ አስቸጋሪ ባሕርይ ሲኖር በባለሙያ ታይቶ ነው ብለዋል። ምክረ ሐሳብ ለቴክኖሎጂ ተጋላጭ መሆን ዓለም አቀፋዊ ጉዳይ መሆኑን ገልጸው፤ ለአጠቃቀሙ ጥንቃቄ ማድረግ ተገቢ መሆኑን አስገንዝበዋል። በተለይም በከተሞች አካባቢ ልጆች እንዳይረብሹ በሚል ሞባይል፣ ቴሌቪዥን፣ ታብሌትን እንደ ሞግዚት የመጠቀም ልማድ መኖሩን አንስተዋል። ይህም በልጆች ጤና ላይ ጉዳት እንደሚያስከትል ወላጆች (ሠራተኞች፣ ሞግዚቶች) መገንዘብ ይኖርባቸዋል ነው ያሉት። ምንም እንኳን በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጠና ጥናት ባይኖርም፤ ከዲጂታል አማራጭና አቅርቦት አኳያ በከተሞች ለቨርቹዋል ኦቲዝም የመጋለጥ ሁኔታው ሰፊ እንደሆነ ይታመናል ሲሉም አመላክተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #የጤና_ነገር #ኦቲዝም #ቨርቹዋል
የከተማ ግብርናን ከጤና ሙያው ጋር ያጣመረው ወጣት
May 14, 2026 8367
በቀደሰ ተክሌ (ከሚዛን አማን) የሰው ልጅ የሕይወት ኡደት በጊዜ የታጠረ ነው። የሰውነት ሚዛን ተለክቶ ውብ ሆኖ የሚገኘው ደግሞ በዚህ የጊዜ ምጣኔ ውስጥ ስኬታማ ሥራ ሰርቶ ተገቢው ቦታ ላይ ሲገኙ ብቻ ነው። ጠንካራ ሰዎች በዕድሜ ዘመናቸው የተሰጣቸውን ጊዜ በአግባቡ ተጠቅመው ስኬት ላይ ይደርሳሉ። ለጊዜ ብዙም ትርጉምና ዋጋ የማይሰጡ ሰዎች ደግሞ እንቅስቃሴያቸውን በጊዜ ስለማይገደብና በዚያው ልክ ተሯሩጠው ስለማይሰሩ ስኬታማ ሳይሆኑ ዘመናቸውን በችግር ያሳልፋሉ። ሰው ሲፈጠር ይህን በማመዛዘን የተሻለውን መንገድ ይጠቀም ዘንድ ደግሞ አዕምሮ ተሰጥቶታል። ማንም ሰው በኑሮ ከመመራት ይልቅ ራሱ ኑሮን መምራት የሚችለው ጠንክሮ ሲሰራ ነው። የአንድ ጠንካራ የሥራ ሰው አንዱ መለኪያ ደግሞ የጊዜ አጠቃቀሙ ነው። ጊዜውን በማብቃቃት ካለው ሥራ ተጨማሪ ሥራ ፈጥሮ የሚሰራና ለበለጠ የሚተጋ ስኬታማ ሕይወትን መምራት ይችላል። በሚዛን አማን ከተማ ኢዜአ ያነጋገርው ወጣት ይህን በተግባር በማረጋገጥ ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን ነው። ወጣት ዳዊት ባይቴንስ ይባላል። ከተሰማራበት የጤና ዘርፍ ጎን ለጎን ባለው ትርፍ ጊዜ በከተማ ግብርና ሥራ ተሰማርቶ ተጠቃሚነቱን እያሳደገ ይገኛል። ሰርቶ ለመለወጥ ካላው ፍላጎትና ቁርጠኝነት የተነሳ በሕይወቱ ምንም አይነት ጊዜ እንዲባክንበት አይፈልግም። እያንዳንዷን ሰዓትና ደቂቃ ትርጉም ባለው መልኩ ለሥራ ያውላል። ይህ የመነጨው ደግሞ ከሥራ ወዳድነቱ ነው። ሲሰራ ውሎ ሲሰራ ቢያድር ደከመኝና ሰለቸኝን አያውቅም። ለእዚህ ባህሪው እርሾ የሆነው ደግሞ በልጅነቱ ወላጆቹን በግብርና ሥራ እያገዘ ማደጉ ነው። በትምህርቱም ወደ ኋላ ሳይል ጠንክሮ በመማር ስኬታማነቱን አስመስክሯል። የኮሌጅ ትምህርቱን በፋርማሲ የተመረቀው ወጣቱ በአሁን ወቅት በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ ቲቺንግ ሆስፒታል በጤና ባለሙያነት እየሠራ ይገኛል። የጤና ተቋም ሥራው ቀንና ማታ በፈረቃ የሚሰራ በመሆኑ ከሆስፒታል ሥራው ውጪ ሲሆን ከተማ ወጥቶ በመዝናናት አሊያም በዋዛ ፈዛዛ የሚያሳልፈው ጊዜ የለውም። ከጤና ሥራው ጎን ለጎን በቤቱ ዙሪያ ያለውን ባዶ መሬት እያለማ ይገኛል። የከተማ ግብርናና የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቮችን ተከትሎ በተለይ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ ይህን የግብርና ልማት ስራውን አጠናክሮ ቀጥሏል። የግብርና ሥራውን የጀመረው በጤና ሙያ ሥራው በወር ከሚያገኘው ደመወዝ ባሻገር ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ለማግኘት አስቦ ነው። "የግብርና ምርቱ ለቤት ውስጥ ፍጆታ ባውለው እንኳ ወጪዬን ይቀንሳል" የሚለውም ሌላው መነሻ ምክንያቱ ነበረ። በዚህም ባለው ጠባብ መሬት ላይ ቆስጣ፣ ጥቅል ጎመን፣ ካሮትና መሰል የጓሮ አትክልቶችን አልምቶ በመጠቀም "ምግቤን ከጓሮዬ" የሚለውንም ንቅናቄ በተግባር አሳይቷል። በጓሮ ያለማቸውን ምርቶች ለቤተሰብ ፍጆታ ማዋሉም ከወጪ እንደታደገው ነው የገለጸው። የአካባቢው መሬት ያለስስት ከሚያበቅላቸው ፍራፍሬዎች መካከል ሙዝ በቀዳሚነት ይጠቀሳል። ወጣት ዳዊትም በጓሮ አትክልት የጀመረውን ሥራ በማስፋት በቤቱ ዙሪያ የሙዝ ልማት ስራውን አጠናክሯል። የሙዝ ምርቱም ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለገበያም እያቀረበ ነው። ዛፉም ጥላ ሆኖ እያገለገለው ነው። ሁሌም ለተጨማሪ ሥራ የሚተጋው ይህ ባለ ራዕይው ወጣት ምርጥ የቡና ዘር ከግብርና ባለሙያዎች በመውሰድ ችግኝ አዘጋጅቶ ለአርሶ አደሮች ያሰራጫል። አምና የቡና ችግኝ ተከላ ወቅት ከ15 ሺህ በላይ የቡና ችግኞችን በጓሮው አዘጋጅቶ በመሸጥ ተጠቃሚ ሆኗል። ከጓሮ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ባሻገር በቆሎ በማልማትም ተጠቃሚነቱን እያሳደገ ነው። ወጣት ዳዊት ባለው ጠባብ የከተማ ማሳ ላይ እነዚህን ልማቶች እያከናወነ ያለው በአንድ ጊዜ አይደለም። እንደ የአዝመራው ተስማሚነት አፈራርቆ የማልማት ጥበብንም ተክኗል። በቆሎ ደርሶ የተነሳበት ማሳ ላይ ሌሎች አትክልቶችን ያለማል። በሌላ በኩል ደግሞ ጥምር የእርሻ ሥርዓትን በመከተል በሙዝና ሌሎች ፍራፍሬዎች ስር ባለ ክፍት ቦታ ላይ ቡና ያለማል፤ የአትክልት ችግኞችንም ያዘጋጃል። ይህ ብልህነት የተሞላው የከተማ ግብርና ልማት ሥራው የከተማ ቤቱን የገጠር ሞዴል አርሶ አደር ማሳ አስመስሎታል። ወደፊት የተቀናጀ የግብርና ልማት ጣቢያን የመፍጠር ዓላማ እንዳለው የገለጸው ወጣቱ፣ በቅርቡም በንብ ማነብ ሥራ ውስጥ ለመሰማራት እየተዘጋጀ መሆኑን ነው የተናገረው። ለዚህም የቀፎ ግዥና የቀፎ ማስቀመጫ ቦታ ዝግጅት ሥራ ላይ ይገኛል። በአሁኑ ወቅት በገበያ እየታየ ያለውን የዋጋ ንረት መቋቋም የሚቻለው ሰርቶ ውጤታማ ሲኮንና ገቢን ማሳደግ ሲቻል ነው የሚል እምነት አለው። ወጣቱ እንደሚለው ምርት የሚያመርት ሰው እየበዛ ሲመጣ ገበያው ይረጋጋል። በመሆኑም ሰዎች ሁሉንም ነገር ከገበያ ከመግዛት ይልቅ ባላቸው ትንሽ መሬት ላይ የተወሰነ ምርት በማምረት ለቤት ውስጥ ፍጆታ እንዲጠቀሙ ይመክራል። ከመደበኛ የመንግሥት ሥራው ጎን ለጎን የተሰማራበት የከተማ ግብርና ልማት ሥራ ወጪውን ከመቆጠብ አልፎ ተጨማሪ ገቢ እያስገኘለት በመሆኑ በቀጣይም ልማቱን ለማጠናከር ሞራል እንደሆነው ተናግሯል። እሱ እንደሚለው ከሆነ በአካባቢው በርካታ ወጣቶች የቤተሰቦቻቸውን ማሳ ትተው በከተማ ያለ ሥራ ጊዜያቸውን ሲያሳልፉ ማየት የተለመደ ነው። ነገር ግን ነገን የተሻለ ለማድረግ ዛሬ የወጣትነት ጊዜን ጠንክረን ልንሰራ ይገባል ይላል። ወጣቶችም ያላቸውን ጉልበትና ጊዜ በመጠቀም ሀብት ማፍራት የሚያስችላቸውን ሥራ መሥራት እንዳለባቸው ይመክራል። በተለይ የእርሻ መሬት ያላቸው ወጣቶች በግብርና ሥራ ራሳቸውን መለወጥ፣ ቤተሰቦቻቸውን መመገብ፣ ገበያ ማረጋጋትና በሀገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ውስጥ አሻራቸውን ማሳረፍ እንዳለባቸው ነው የገለጸው። የሚዛን አማን ከተማ ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ኅብረት ሥራ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዘሪሁን መንግሥቱ የወጣት ዳዊት ታታሪነት ለብዙዎች ተሞክሮ እንደሚሆን ነው የገለጹት። በተለይ የከተማ ግብርናና የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቮችን መሠረት በማድረግ ያከናወናቸው ተግባራት በትንሽ መሬት መስራት ከተቻለ ገበያን ማረጋጋት እንደሚቻል በተግባር ያሳየ ነው ብለዋል። ጽህፈት ቤቱ ወጣቱንና የእሱን ፈለግ ተከትለው የሚሠሩ ወጣቶችን ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጠዋል። ኃላፊው እንዳሉት በአሁኑ ወቅትም በሌማት ትሩፋት የሥራ ዘርፎች ወጣቶች በብዛት እንዲሰማሩ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በራስ ተነሳሽነት ያላቸውን ጊዜ አብቃቅተው ወደልማት የገቡ እንደ ወጣት ዳዊት ያሉ ወጣቶች ቢበራከቱ ለግብርናው ዘርፍ ኢኮኖሚ የሚኖራቸው አዎንታዊ ሚናም የጎላ ነው። ማንም ሰው ኑሮን አሸንፎ ወጤታማ ለመሆን እንደ ወጣት ዳዊት በሥራ መትጋት ይኖርበታል። ወቅቱ ያለን ጊዜ አብቃቅቶ ተጨማሪ ሥራዎች መስራት የግድ የሚልበት ወቅት ነው። ለብዙዎች በቅጥር ሰርቶ በሚገኝ ገቢ ብቻ የሚፈለገውን ለውጥ ለማምጣት አስቸጋሪ በመሆኑ አማራጮችን መጠቀም ያስፈልጋል። ለእዚህም እንደወጣት ዳዊት በዙሪያችን ምን ሀብት አለ በሚል ለይቶ ጥቅም ላይ ማዋል ያስፈልጋል። ጊዜን ከጉልበት ጋር አጣምሮ መጠቀምም እንዲሁ ትኩረት ልንሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው። የሰው ልጅ በሕጻንነትና በእርጅናው ዕድሜ የፈለገውን ማድረግ፣ ወጥቶና ወርዶ ሀብት ማፍራት አይችልም። ይህ የሚሆነው በወጣትነትና በጎልማሳነት ዕድሜ ብቻ ነው። በመሆኑም ለነገ ያለምነውን በጊዜው ማሳካት የምንችለው ዛሬ ጠንክረን ስንሰራ ነው። ስለዚህ የወጣትነት ዕድሜያችንን በውጤት ለማጀብ ጠንክረን ልንሠራበት ይገባል። ሥራ ክቡር ከመሆን በላይ ጠንክሮ የሰራውንም ያስከብራል፤ ይለውጣል፤ ሰላም !
አዲስ ምዕራፍ- ከዜጎች ደጃፍ እስከ እጅ ስልክ
Apr 25, 2026 4281
አዲስ ምዕራፍ- ከዜጎች ደጃፍ እስከ እጅ ስልክ በቁምልኝ አያሌው በአንድ ሀገር ሁለንተናዊ ዕድገት ውስጥ የመንግሥት አገልግሎት ጥራት ከሰው ልጅ የደም ዝውውር ጋር ይመሰላል። በሌላ በኩልም፣ የአገልግሎት አሰጣጥ የዜጎች የሞራልና የፍትሕ ልዕልና መለኪያ ተደርጎ ይወሰዳል። መንግሥት ለዜጎቹ የሚያቀርባቸው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶች ጥራት፣ ፍጥነትና ፍትሐዊነትም የሀገርን ፖለቲካዊ መረጋጋትና የኢኮኖሚ አቅጣጫ የሚበይኑ መጋቢዎች ናቸው። ታዋቂው የፖለቲካል ኢኮኖሚ ምሁር ፍራንሲስ ፉኩያማ እንደሚሉት፤ "የመንግሥት ተቋማት ብቃት (State Capacity) ለኢኮኖሚ ዕድገትና ለዴሞክራሲ መረጋጋት መሠረት ነው።" መልካም አስተዳደር የሰፈነበት ሥርዓት የሕዝብ አመኔታን በመጨመርና ማህበራዊ እኩልነትን በማስፈን ለዘላቂ ሰላም የማይተካ ሚና ይጫወታል። ይህም ሀገርን በኢኮኖሚ ለማሳደግና ለማበልጸግ በሚደረገው ርብርብ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። ሌላኛው የኢኮኖሚክስ ምሁር ጆሴፍ ስቲግሊዝ በበኩላቸው፤ "ውጤታማ መንግሥት ማለት ዜጎቹን በግልጽነትና በተጠያቂነት የሚያገለግል፣ በሂደቱም የህዝብ አመኔታን መገንባት የሚችል ነው" ሲሉ አጽንኦት ይሰጣሉ። በአንፃሩ፤ የአገልግሎት ክፍተትና የአስተዳደር ጉድለት ለሀብት ብክነት፣ ለሙስና እና ብልሹ አሰራር በር በመክፈት ዜጎችን ለከፍተኛ ምሬት በማጋለጥ አመኔታን ያሳጣል። ይህንን እንግልት ለማቃለል ሀገራት አገልግሎትን የሚያዘምን ፈጣንና ቀልጣፋ የዲጂታል ሥርዓት እየዘረጉ ይገኛል። ኢትዮጵያም ይህንን መርህ በመከተል ዘገምተኛ አሰራር ከወለደው የ"እጅ መንሻ" (ሙስና) ልምምድ በመላቀቅ ዘመናዊና ግልጽ የዲጂታል ሽግግርን በማፋጠን ላይ ትገኛለች። ይህም ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባትና ሉዓላዊነትን የሚያጎናጽፍ ወሳኝ የልማት ምኅዳር እየፈጠረ ነው። የመደመር መንግሥት ዕሳቤ፤ በተቋማት ግንባታና አገልግሎት ጥራት!! በመደመር ፍልስፍና ውስጥ የመንግሥት ተቋማት ግንባታ የሀገር ግንባታ የጀርባ አጥንት ተደርገው ይወሰዳሉ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በመደመር መንግሥት መጽሐፋቸው ገፅ-129 እንዳሰፈሩት፤ ''የመደመር መንግሥት ከውስብስብ ቢሮክራሲ ተላቀው የመደመር ለውጥ የሚያመጡ ተቋማት ውቅር ነው። በመሆኑም ተቋማት ከተለመደ ''የሥራ ሂደት መር'' አካሄድ መላቀቅ ይጠበቅባቸዋል። አደረጃጀታቸውንም ለሚያገለግሉት ሕዝብ ትርጉም ያለው ለውጥ እንዲያገኙ ወደሚረዳቸው አደረጃጀት መሸጋገር አለባቸው። ለመደመር መንግሥት ሕዝቡን ማገልገል ከቢሮክራሲ በላይ ነው'' በሚል አስገንዝበዋል። ለዚህም ነው ተቋማት የሰውን ልጅ አቅምና ዕውቀት አቀናጅተው ለጋራ ዓላማ የሚያውሉ ሕያው መዋቅሮች ናቸው የሚባለው።   በመደመር ዕሳቤ ጠንካራ ተቋማት ማለት በግለሰቦች ፍላጎትና ስሜት ላይ ያልተመሰረቱ ይልቁንም በሕግና በሥርዓት የሚመሩ መሆን አለባቸው። በመደመር መንግሥት መፅሐፍ ገፅ-130 እንደሰፈረው፤ ''በየተቋማት ያሉ የመንግስት ሠራተኞች ሕዝቡን ከቢሮክራሲው በላይ የሚመለከቱ እንዲሆኑ ይጠበቃል። አገልጋይነትን የተላበሱ መሆን ይጠበቅባቸዋል።'' መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትም ይህንን ዕሳቤ በተግባር የሚተረጉም ነው። ግለሰባዊ ንክኪን በመቀነስና አሰራርን በቴክኖሎጂ በመተካት ተቋማት ከግለሰቦች መልካም ፈቃድ ይልቅ በሥርዓት ወደሚመራ ተቋማዊ ብቃት መሸጋገርን ያሳያል። የአገልግሎት ጥራትና የዜጎች ክብር በመደመር መንግሥት ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ሰው ተኮር የልማት ነጥብ ነው። ''ለሕዝቡ ቅድሚያ የማይሰጥ አመራርም ሆነ ሠራተኛ የመደመር መንግሥት ወገን አይደለም። እንዲህ ዓይነቱን ግለሰብም ሆነ አይቶ እንዳላየ በማለፍ የማይታገል ሰው በመደመር መንግሥት ውስጥ ዕድል ፈንታ የለውም'' በሚል በመደመር መንግሥት መፅሐፍ የሰፈረው ግልፅ መልዕክትም መንግሥት የአገልጋይነት እንጂ የገዥነት መንፈስ ሊኖረው እንደማይገባ በጉልህ ያመላክታል። የአገልግሎት ጥራት መሻሻልም ዜጎች በሀገራቸው ተቋማት ክብራቸውና መብታቸው ተጠብቆ ያለ እንግልት የሚገለገሉበትን ምኅዳር ይፈጥራል። በተቋማት አገልግሎት የዜጋ እርካታ (Citizen Satisfaction) ዋነኛ የፖለቲካል ኢኮኖሚ ዕድገት ምንጭ ተደርጎ ይወሰዳል። በመደመር መንግስት ዕይታ የብልሹ አሰራር መታገያ ስትራቴጂ በጩኸትና በቅጣት ብቻ የሚመጣ ሳይሆን አሰራርን በማዘመን ጭምር ነው። የመሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎትም ሌብነትን የማይጋብዝ ሥርዓት የፈጠረ (Systemic Prevention) ስትራቴጂክ አቅጣጫ ሆኗል።   የኢትዮጵያ የዲጂታል ልማትና የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የመደመር መንግሥት መሠረታዊ የተቋማት ሪፎርም ትግበራን (Institutional Reform) የሚያሳዩ ናቸው። ይህም ተቋማትን ከመዋቅራዊ ሽግግርና ለውጥ ባለፈ የተቋማት ሠራተኞችን ከመንግሥት ሠራተኛነት ወደ ሕዝብ አገልጋይነት የአስተሳሰብ ለውጥ (Paradigm Shift)፣ ኋላ ቀር አሰራርን በዲጂታል የቴክኖሎጂ አማራጭ የሚተካ (Technology Integration)፣ አገልግሎትን ለሁሉም ዜጋ በእኩልነት፣ በቅርበትና ፍትሐዊነት የማዳረስ ፅንሰ ሃሳባዊ ግብን በተግባር ያረጋገጠ ሆኗል። ይህ ታላቅ ተግባርም ኢትዮጵያ በመደመር ዕሳቤ የጀመረችውን የብልፅግና ጉዞ የሚያፋጥንና ዜጎች በመንግሥታቸው ላይ ያላቸውን አመኔታ በጽኑ መሠረት ላይ የሚገነባ መሠረት ነው። የዲጂታል ኢትዮጵያ ርዕይና ስትራቴጂክ ሽግግር!! ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ለግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝምና አይሲቲ ዘርፎች ወሳኝ የልማት ዕድሎችን ፈጥሯል። በዚህ ሰፊ መርሃ ግብር ውስጥ የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ እንደ ዋነኛ የብልፅግና ምሰሶ ተወስዷል። በ"ዲጂታል ኢትዮጵያ-2025" ስትራቴጂ የተጀመረውና በስኬት የተጠናቀቀው ጉዞ ዛሬ ላይ ሀገሪቷን ወደ "ዲጂታል ኢትዮጵያ-2030" አሸጋግሯታል። ይህ ስትራቴጂ ዜጎች ካሉበት ቦታ ሆነው አገልግሎት የሚያገኙበትን ምኅዳር በመፍጠር በሰው ንክኪ የሚፈጠሩ ብልሹ አሰራሮችንና የአገልግሎት እንግልትን በማስቀረት ረገድ ታሪክ ቀያሪ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። የልማትና ዕድገት ምሁሩ አማርትያ ሴን፤ "ልማት የሰው ልጅ ምርጫና የመገልገያ አቅሙን ማስፋፊያ መሣሪያ ነው" በማለት የሚገልጹት ስለልማት ከፍ ያለ ትርጉም ይሰጠናል። የኢትዮጵያ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትም ዜጎች የሚያጋጥሟቸውን እንግልቶች በማስወገድ ትኩረታቸውን በልማት ላይ እንዲያደርጉ በማስቻሉ፣ ይህንን የልማት ፅንሰ-ሃሳብ በተግባር እየተረጎመ ይገኛል።   የአንድ ጣሪያ በረከትና የቅልጥፍና ተምሳሌት - መሶብ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሚያዚያ 18/2017 ዓ.ም የተመረቀው የፌዴራል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ ለተቋማዊ ሽግግር መነሻ ሆኗል። ቁልፍ የመንግሥት አገልግሎቶች በአንድ ጣሪያ ስር መሰባሰባቸው የአገልግሎት አሰጣጥ ጥራቱን ወደ ከፍተኛ ደረጃ አሸጋግሮታል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ እንደገለጹት፤ ይህ ማዕከል ዜጎች ጊዜያቸውንና ሀብታቸውን በመቆጠብ ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኙ በማድረግ ለዘመናት የቆየውን ምሬት የሚቀለብስ የሪፎርም እርምጃ ነው። በወቅቱ ሲጀመር 12 የነበሩት ፌዴራል ተቋማት፤ አሁን ላይ 23 በመሻገር አገልግሎታቸውን እየሰጡ ይገኛል። ይህም የዜጎች እንግልት በማስቀረት ታላቅ እፎይታን ፈጥሯል። እነዚህ ተቋማት፦ የብሔራዊ መታወቂያ፣ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት፣ የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት፣ የገቢዎች ሚኒስቴር፣ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር፣ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር፣ የኢንቨስትመንት ኮሚሽን፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ የትምህርት ስልጠና ባለስልጣን፣ ኢትዮ ፖስታ፣ ኢትዮ ቴሌኮም፣ የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን፣ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን፣ የኢትዮጵያ ምግብና መድኃኒት ባለስልጣን፣ የኢትዮጵያ ግብርና ባለስልጣን፣ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ባለስልጣን፣ የኢትጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን፣ የጤና ሚኒስቴር፣ የፍትሕ ሚኒስቴር፣ ቱሪዝም ሚኒስቴር፣ የትምህርት ምዘናና የፈተናዎች አገልግሎት ናቸው። መነሻውን አዲስ አበባ ከተማ የፌዴራል ተቋማት በአንድ በማሰባሰብ የጀመረው ይህ አገልግሎት አሁን ላይ በሁሉም ክልሎችና በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች ተደራሽ እየሆነ ነው። ይህም የመልካም አስተዳደር እጦትን የሚያቃልል ታሪክ ቀያሪ መደላድል ፈጥሯል። አዲስ መሶብ - የተንቀሳቃሽ አገልግሎት ተስፋ!! በመዲናችን ሚያዚያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም በይፋ የተጀመረው መሶብ የአንድ ማዕከል ተንቀሳቃሽ አገልግሎት፣ "መንግሥት ወደ ዜጋው ይሄዳል" (Citizen-Centric Governance) የሚለውን የዘመናዊ አስተዳደር ፍልስፍና በተግባር ያሳየ ነው። በፀሐይ ኃይልና በፈጣን ኔትወርክ የታገዘው ይህ ተንቀሳቃሽ አገልግሎት የስምንት ተቋማትን 36 ዓይነት አገልግሎቶች ወደ ህዝቡ ደጃፍ በማምጣት ረገድ ተምሳሌት ሆኗል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በወቅቱ እንደገለጹት፤ ከተማዋ ለዘመናት ስር በሰደደ የአገልግሎት አሰጣጥ ችግር ተተብትባ ብትቆይም፣ የመሶብ ዲጂታል አገልግሎት ግን ለተገልጋዩ እውነተኛ እፎይታን ይዞ መጥቷል። የቀጣዩ ዘመን ግብ - አገልግሎትን በእጅ ስልክ!! ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቀጣይ አገልግሎቱን ወደ ዜጎች የእጅ ስልክ የማሸጋገር ግብ መኖሩን አረጋግጠዋል። ይህ ሽግግር ሙሉ በሙሉ ስኬታማ እንዲሆን የዲጂታል መታወቂያ ወሳኝ ሚና ይጫወታል። ዜጎችን በዲጂታል መታወቂያ መለየት መቻሉ የአሰራር ግልጽነትን ከመጨመሩም በላይ መንግሥት አገልግሎቱን ለማን እየሰጠ እንደሆነ በትክክል እንዲያውቅ ያስችለዋል።   ተገልጋይን አክብሮ፣ ስርቆትና "እጅ መንሻን" አስቀርቶ አገልግሎት መስጠት የባህል ለውጥ ይጠይቃል። ለዚህም ሲቪል ሰርቪሱን በማዘመን፣ ቴክኖሎጂንና የባህል ለውጥን በማቀናጀት የእጅ መንሻን ባህል የሚያስቀር መሠረት እየተጣለ ይገኛል። ለዚህ ለውጥ ስኬት እያንዳንዱ ዜጋና ተቋም የበኩሉን ሊወጣ ይገባል። በአጠቃላይ የኢትዮጵያ የዲጂታል ልማት መርሃ ግብርና የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ሙስናን በማድረቅ ፍቱን መፍትሔ እየሰጡ ይገኛሉ። ይህም ሀገሪቷን ከቆየችበት የ"እጅ መንሻ" አዙሪት አውጥቶ፣ ተቋማት ለዜጎች ክብር ወደሚያሳዩበት አዲስ ምዕራፍ አሸጋግሯታል። ይህ ጉዞ እመርታ ነው፤ ግልጽነትን በማንገስና የህዝብን እርካታ በመጨመር የብልጽግና ጉዞውን የሚያፋጥን ነው።
ፋሲካ -አብሮነት የሚደምቅበት የደስታ በዓል
Apr 12, 2026 1569
በኢትዮጵያ የፋሲካ በዓል በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በታላቅ ድምቀት የሚከበር በዓል ነው። የትንሳኤ በዓል የሚከበረው ከ55 ቀናት የጾም ወቅት በኋላ ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ እምነት ተከታዮች እነዚህን ቀናት ፈጣሪያቸውን በጾምና ጸሎት ከመለመን ባለፈ ከሥጋ፣ ከወተትና መሰል የእንስሳት ተዋጽኦ ምግቦች ታቅበው ነው የሚያሳልፉት። የትንሣኤ በዓል ከመድረሱ በፊት ያለው አንድ ሳምንት "ሰሞነ ሕማማት" በመባል ይታወቃል። የእምነቱ ተከታዮች በሰሞነ ሕማማት ኢየሱስ ክርስቶስ ያሳለፈውን መከራና ስቃይ በማሰብ በቤተ ክርስቲያን በስግደት፣ በጸሎትና በጾም በተለየ ሁኔታ ያሳልፋሉ። ምእመናን በእለተ አርብ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች መዳን ብሎ በቀራኒዮ አደባባይ የከፈለውን መከራ፣ ግርፋትና ስቅላት በማሰብ በስግደት፣ በጸሎትና በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስርዓቶች ያሳልፋሉ። የትንሳኤ (የፋሲካ) በዓልም ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትል ድል አድርጎ መነሳቱን ተከትሎ የሚከበር ነው። ትንሳኤው ይቅርታ፣ ለሰው ለጆች መዳን የተከፈለ ፍቅርና መስዋዕትነት ጎልቶ የሚታይበት ነው። በመሆኑም ፋሲካ ሞትን ድል በመንሳት በትንሳኤ የምስራች የተበሰረበት ታላቅ በዓል ነው ማለት ይቻላል። ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በትንሳኤ የለወጠበት ለሰው ልጅም ፍቅርን በቤዛነት ተክቶ ያሳየበት ዕለት ነው። ዕለቱ ትንሳኤ ብርሀን የታየበት በመሆኑ በትንሣኤ ዋዜማ ቅዳሜ ምሽት ምዕመናን ነጭ ልብስ ለብሰው ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ሌሊቱን በጸሎትና በተለያዩ ሃይማኖታዊ ስርአቶች ያሳልፋሉ። የሌሊቱ ቅዳሴና ስርአተ ፀሎት ከተጠናቀቀ በኋላ ምዕመናን ወደ ቤታቸው ሲመለሱ ጾም ይፈታሉ። ከቅባት ምግቦች ለሁለት ወራት በመቆጠብ ያሳለፉበት ወቅት በመሆኑም በትንሳኤ ሌሊት ዶሮ በመብላት ጾማቸውን ይፈስካሉ። በበዓሉ ቀንም በነጭ የሀበሻ ልብስ ደምቀው ይታያሉ። በዓሉ ከሃይማኖታዊ ሥርአቱ ባለፈ የአብሮነት፣ የፍቅርንና የመተሳሰብ እሴት ያለው ነው። ዘመድ አዝማድ በመጠራራትና ከጎረቤት ጋር አብሮ በመብላትና በመጠጣት የሚያሳልፉት ነው። ቤት ያፈራውን በመቋደስ በዓሉን በአብሮነት በደስታ ያሳልፋሉ። የፋሲካ በዓል ማህበራዊ ትስስር የሚገለጥበትና አብሮነት የሚደምቅበት የደስታ በዓል ነው። በተለይ በፋሲካ በዓል ለዶሮ ወጥ ልዩ ትኩረት ይሰጣል። ፋሲካና ዶሮ ወጥ ጥብቅ የሆነ ባህላዊ ቁርኝት ያላቸው በመሆኑ አንዱ የበዓሉ ማድመቂያ ተደርጎ ይወሰዳል። ከዚህ በተጨማሪ የበሬ ቅርጫ፣ በግ፣ ፍየል፣ ዳቦና ጠላ እንደየ አቅም በማዘጋጀት ይከበራል። በአንዳንዶች ዘንድም ከገብስ ብቻ የሚዘጋጅ "ኬኔቶ" የተሰኘ (ከአልኮል ነፃ የሆነ መጠጥ) በማዘጋጀት በአማራጭነት ይቀርባል።
በኅብረትና ጽናት የሚቀረጽ ብርሃን፤ የኢትዮጵያ ትንሣኤ
Apr 12, 2026 1294
በኅብረትና ጽናት የሚቀረጽ ብርሃን፤ የኢትዮጵያ ትንሣኤ በቀበኔሳ ገቢሳ ትንሣኤ ለሰው ልጅ ተስፋን፣ ዘለዓለማዊ ሕይወትን እና ከኃጢአት ነፃ መውጣትን የሚያበስር ኃይማኖታዊ በዓል ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ በመነሳቱ የሰው ልጅ የዘለዓለም የሕይወት አክሊልን ተስፋ ያደረገበት፣ የእግዚአብሔር ፍቅር የተገለጠበት እንዲሁም የሰው ልጅ ከዘለዓለም ሞትና ከኃጢአት ባርነት ነፃ የወጣበት የድኅነት፣ የፍቅር፣ የጽናትና የተስፋ ብርሃን ብስራት ነው፡፡ የትንሣኤ በዓል ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ የመነሳቱ ታላቅ ምሥጢር የሚታሰብበት ብቻ አይደለም፤ ይልቁንስ የሰው ልጅ ከውርደት ወደ ክብር፣ ከኃጢያት ባርነት ወደ ድኅነት እንዲሁም ከጉስቁልና ወደ ብሩህ ተስፋ የተሸጋገረበት የድል አዋጅ ነው። በዕለቱም በሞት ላይ ሕይወት፣ በሐዘን ላይ ደስታ፣ በቂም ላይ ይቅርታ ተበስሮበታል። ከበዓላት ሁሉ የላቀ የነጻነት ተምሳሌት ነው ትንሣኤ። 👉የትንሣኤ ሕያው አስተምሮ በዕለት ተዕለት ሕይወት ትንሣኤ ሲከበር ከሥርዓተ አምልኮ ባለፈ፣ በዓሉ የሚሰጠውን ታላቅ አስተምሮ ማጤን ይገባል። ትንሣኤ በየቀኑ ካለንበት ድካምና ውድቀት በአዲስ መንፈስ የመነሳት አቅም ነው። በዓሉ የሚያስተምረንን የጽናት፣ የተስፋና የአብሮነት ዕሴት በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ መኖር ያስፈልጋል። ለዚህም የተቸገሩን መርዳት፣ የታመሙትን መጠየቅና የተጣሉትን ማስታረቅ የበዓሉን ትርጉም እውነተኛ ያደርገዋል። 👉የኢትዮጵያ ትንሣኤ፤ በፈተና የጸና ብርሃን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዓሉን በማስመልከት ባስተላለፉት መልዕክት፤ "የዘንድሮውን የትንሣኤ በዓል የምናከብረው ሀገራችን ኢትዮጵያ በፈታኝ የታሪክ ምዕራፍ ውስጥ ሆና እያለች ነው። መንገዳችን ረጅም፣ ጉዟችንም እሾህ የበዛበት ሊሆን ይችላል። ብርሃን እንዳናይ የሚጋርዱ፣ በጨለማ ወጥመድ ሊያሥሩን የሚሞክሩ መሰናክሎች ቢበዙም፣ እምነታችን ግን ከሕማማት በኋላ ትንሣኤ እንደሚመጣ ነው" ብለዋል፡፡ "ኢትዮጵያ ዛሬም ትንሳኤዋን እያየች ነው። መቃብሯ ተከፍቷል፤ ማኅተሙም ተሰብሯል። የትንሣኤውን ዜና ሊያደበዝዙ የሚሞክሩ የውሸት ወሬዎችና ተስፋ አስቆራጭ ትረካዎች የሀገራችንን የብርሃን ጉዞ ሊገቱት አይችሉም። ትንሳኤው እውነት ነው፤ ብርሃኑም የማይቀለበስ ሀቅ ሆኗል" ሲሉም አረጋግጠዋል፡፡ 👉ዴሞክራሲ እና ብሔራዊ ምክክር፤ የተስፋ ምዕራፎች የኢትዮጵያ ትንሣኤ አንዱ መገለጫ ዴሞክራሲን የመገንባት ጽናት ነው። ትንሣኤ ያለ ሕማማት እንደማይገኝ ሁሉ ዴሞክራሲ ያለ ፈተና በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ዴሞክራሲ የሚገነባው በጽናት እንጂ በፍርሃት አይደለም። ዴሞክራሲን እየገነባን በትዕግሥትና በቆራጥነት ወደ ተስፋዋ ምድር እንደርሳለን። አሁን ያለው የዓለም ነባራዊ ሁኔታ ጦርነት፣ የኢኮኖሚ ቀውስና ማህበራዊ አለመረጋጋት የትንሳኤን ትምህርት ከመቼውም ጊዜ በላይ አስፈላጊ ያደርገዋል፡፡ ችግሮችን በብቸኝነት የምንወጣበት ጊዜ አብቅቷል። ዛሬ እንደህዝብ የሚያስፈልገን ከ"እኔ" ወደ "እኛ" መሸጋገር፣ የግል ፍላጎትን ለጋራ ስኬት መስዋዕት ማድረግ ግድ የሚልበት ወቅት ላይ ነን። የአንድነት ጉዟችንን በማጠናከር ዓለም አቀፋዊና ሀገራዊ ጫናዎችን ለመቋቋም በጋራ መቆም ይገባናል። የተቸገሩትን በመርዳት፣ የታመሙትን በመጠየቅና የተጣሉትን በማስታረቅ የተግባር አብሮነትን በማሳየት የበዓሉን እውነተኛ ትርጉም መግለጥ ይገባል፡፡ 👉ምርጫ፤ ከኢትዮጵያን ትንሣኤ ማብሰሪያዎች አንዱ ምዕራፍ ትንሣኤ ሞት ድል የተነሳበትና ተስፋ የታደሰበት ዕለት ነው። እኛም በምርጫ ካርዳችን የሃሳብ ልዩነትን በዴሞክራሲያዊ አንድነት ድል በማድረግ የኢትዮጵያን የብልፅግና ትንሳኤ እናረጋግጣለን። በትንሣኤ በዓል የምንማረው ይቅርታና ጽናትም ለምርጫችን ስኬት አቅም ይሆናል። በኅብረት የምንሰጠው ድምፅም የነገዋን ብሩህ ኢትዮጵያ የመቅረጽ ኃይል በእጃችን መሆኑን ያሳያል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በመልዕክታቸው "ምርጫ የኢትዮጵያን ትንሣኤ ማብሰሪያዎች አንዱ ምዕራፍ ነው። ትንሣኤን ያለ ሕማማት እንደማናስበው ሁሉ ዴሞክራሲንም ከውጣ ውረድ ነጥሎ ማየት አይቻልም። በዓለም ላይ በደልዳላ መንገድ ተጉዞ ዴሞክራሲን የገነባ ሀገር የለም። ዴሞክራሲና ብልፅግና ያለ ጽናት አይሳኩም። ከእኛ በፊት ዐመጻውን በትዕግሥት የመከቱ ተሻግረዋል፤ ሑካታውን በጽናት ያለፉ አሳክተዋል። ብንመኝም ፈተናውን አናስቀርም፤ መጽናት ግን እንችላለን። ከድኅነት መውጫው ብርታታችን፣ ወደ ዴሞክራሲ መድረሻችው ትዕግሥታችን እንደሆነ አምነን ለኢትዮጵያ ትንሣኤ በሙሉ ልባችን እንትጋ!!" ብለዋል። 👉የወደፊት እጣ ፈንታችን በእጃችን ከፊታችን የሚጠብቁን ሀገራዊ ምክክርና የ2018 ዓ.ም ጠቅላላ ምርጫ የኢትዮጵያን የወደፊት መጻኢ ዕድል የሚወስኑ ታላላቅ ሁነቶች ናቸው። እነዚህ ሂደቶች ስኬታማ የሚሆኑት እያንዳንዱ ዜጋ የድርሻውን ሲወጣ ብቻ ነው። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር በልባችን ውስጥ ይቅርታና አብሮነት ሲነግስ ብቻ ግቡን ይመታል። ትንሣኤ ሞት ድል የተነሳበት እንደሆነው ሁሉ፣ በምክክሩም ጥልን፣ ጥርጣሬን፣ ያለመግባባት መንፈስን ድል መንሳት ይገባል፤ ቅንነት፣ ተስፋና መተሳሰብ ለምክክሩ ስኬት የመተማመኛ ቁልፎች ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ጠቅላላ ምርጫ 2018 ዓ.ም ደግሞ የዜጎች ዴሞክራሲያዊ ተሳትፎ ማሳያ አንጓ ነው፤ የዜጎች ነፃ ተሳትፎ መብታቸውን የሚያስከብሩበት ፍላጎታቸውን የሚያረጋግጡበት ማረጋገጫ ማህተም ጭምር፡፡ ዜጎች የመምረጥና የመመረጥ መብታቸውን የሚያስከብሩበት፤ የሌላውን ሃሳብ አክብረው የራሳቸውን የሚያስከብሩበት ለኢትዮጵያ ትንሣኤ በጋራ የሚቆሙበት መድረክ ነው፡፡ ትንሣኤ የድልና የነጻነት በዓል ነው። ይህንን ታላቅ ዕለት ስናከብር ያለፈውን ቁስል ሽረን፣ ለነገ ተስፋ ሰንቀን መሆን አለበት። እርስ በእርስ በመደጋገፍ፣ ችግሮችን በንግግር በመፍታት ለሀገራዊ ምክክር ሂደቱ ስኬታማነት የድርሻችንን መወጣት ይገባናል። የተሻለችና የበለፀገች ኢትዮጵያን ለመገንባት በጋራ እንቁም! መልካም የትንሳኤ በዓል!!
የመልከ መልካሟ ብዙ መልኮች
Apr 5, 2026 5276
በዮሐንስ ደርበው ✍️ የመልከ መልካሟ ብዙ መልኮች ‘በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ’ ከሚለው ብኂል የላቁና ቁጭት የወለዳቸው ኢኒሼቲቮች - የቱሪዝም ፀጋን ከመግለጥ ባለፈ የገቢ መጠንን እንዲሁም የሥራ ዕድልን እያሳደጉ ነው። ምድረ ቀደምቷ ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ እንደመሆኗ ብዙ ናት። ይህን ሁሉም ሀገራት ስለማያገኙት ዕድለኛም ናት፤ የእኛም ስለሆነች መታደል ነው። የተለያየ የኑሮ ዘይቤ፣ ባህል እንዲሁም ሁሉንም የዐየር ፀባይ ዐቅፋለች። ደግሞም ልዩ ልዩ የተፈጥሮ አቀማመጥ በልዩነት የተቸራት። አሥረጂ ማቅረብ ቢያሻ በሀገሪቱ ከፍተኛ ከሆነው ስሜን ተራራዎች እስከ ዝቅተኛው ስፍራ ዳሎል ያለውን የተፈጥሮ ፀጋ መጥቀስ ሁነኛ ምሥክር ነው። ከሀገራዊ ለውጡ አበርክቶዎች የዘርፉ ባለሙያዎች ‘ካሎሪ አልባው መድኃኒት’ ይሉታል የብርቱዎቹ ልጆች ብርታት በቀጣይ ...! ከመጋቢት ሥጦታዎች መካከል - የጉባ ብሥራቶች ✍️ የተፈጥሮ ችሮታ ለኢትዮጵያ ከብዙ ሥጦታዎቿ መካከል ብሔራዊ ፓርኮችን ብቻ ብናነሳ… የኢትዮጵያ የዱር እንስሣት ጥበቃ ባለሥልጣን በጀት መድቦ በቀጥታ በሥሩ 11 ብሔራዊ ፓርኮችን እና ሁለት የዱር እንስሣት መጠለያዎች ያሥተዳድራል። እነሱም፡- 📌 ስሜን ተራራዎች ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ባሌ ተራራዎች ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 አዋሽ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 አብያታ ሻላ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ነጭ ሳር ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ኦሞ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 አልጣሽ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ገራይሌ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ሃላይደጌ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ቃፍታ ሽራሮ ብሔራዊ ፓርክ እንዲሁም 👉 ባቢሌ የዝሆኖች መጠለያ እና 👉 ሲንቂሌ የቆርኬዎች መጠለያዎች ናቸው። ብሔራዊ ፓርኮቹና የዱር እንስሣት መጠለያዎቹ የሀገሬው ሀብት ናቸውና፤ እየተንከባከቡ መጠቀም ይገባል። ✍️ መንግሥት ለኢትዮጵያ ቱሪዝም ከላይ የተገለጹትን ብሔራዊ ፓርኮችና ሌሎችንም፤ ከቤት እንስሣት ንክኪ ነጻ በማድረግ፣ ከልቅ ግጦሽ እንዲሁም ከሕገ-ወጥ ዐደን ለመጠበቅ መንግሥት ብዙ ገንዘብ ያወጣል። የሰው ኃይልና የቁሳቁስ ዐቅርቦትንም ያሟላል። ይህም ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት ይመሠክራል። የብሄራዊ ቤተ መንግስት ሙዚዬም፣ የጅማ አባ ጅፋር ቤተ መንግስት፣ ሶፍዑመር ዋሻን እና የፋሲል አብያተ መንግሥትን ጨምሮ በየክልሎች የሚገኙ ቅርሶችን እድሳት ተደርጎላቸዋል። በሌላ በኩል የላሊበላ አብያተክርስቲያናት በልዩ ሁኔታ እድሳት በማድረግ እንዲሁ እየተጋ ነው። ከአምስቱ የኢኮኖሚ ምሰሶዎቹ አንዱ የቱሪዝም ዘርፍ ማድረጉም ትኩረቱን ያሳያል። በዚህ ሂደት በየአካባቢው ፀጋዎችን ዕየለየ በርካታ መዳረሻዎችንና የጎብኝ ማረፊዎችን አልምቷል፤ እያለማም ነው። እነዚህም በኢኮኖሚው ብሎም በሥራ ዕድል ፈጠራ ከፍ ያለ ሚና እያበረከቱ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት፤ በገበታ ለሸገር፣ በገበታ ለሀገር እና በገበታ ለትውልድ የተሠሩ መዳረሻዎችን ለአብነት ብንጠቅስ፤ ‘በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ’ ከሚለው ብኂል የላቁና ቁጭት የወለዳቸው ኢኒሼቲቮች ናቸው። የቱሪዝም ፀጋን ከመግለጥ ባለፈ የገቢ ምንጭ እንዲሁምና የሥራ ዕድልን እያሳደጉ ነው። ኢትዮጵያ ዛሬ ነገንም እየሠራች ነውና፤ በቱሪዝሙ ዘርፍ የሚከናወኑ ተግባራት በተለያየ የኢትዮጵያ ክፍሎች መጭውን ትውልድ ባገናዘበ ሁኔታ እየተሳለጡ ነው። በአፍሪካ መዲና በአንድነት እና የወዳጅነት ፓርኮች ጅማሮውን ያደረገው የዘርፉ ልማት፤ ወደ ወንጪ ኢኮቱሪዝም፣ ጎርጎራ፣ ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት፣ የሸበሌ ሪዞርት፣ ሶፍዑመር ዋሻ፣ ባሌ ተራራዎች ብሔራዊ ፓርክ፣ የዝሆኖች ዳና ሎጂ፣ የኒዒን ሌ ፓልም ሎጂ ድረስ ወዘተ… ዘልቋል። እንደቀጠለም ነው። እነዚህም ፀጋን ለይቶ ወደ ሃብት በመቀየር ሂደት በመንግሥት ብርታት የለሙ መዳረሻዎች ናቸው። መንግሥት ነባር መዳረሻዎችን በመጠገንና በማደሥ፤ አዳዲስ መዳረሻ በመገንባት ለኢትዮጵያ ቱሪዝም አልሠሠተም፤ ብዙ እየሠጠ ነው። ✍️ ከቱሪዝም ዘርፍ አንጻር የሕብረተሰቡ ሚና ቱሪዝም በተፈጥሮው ከበርካታ ጉዳዮች ጋር ይተሣሠራል። በእጅጉ ሰላም ይሻል፤ የሰላም ባለቤት ደግሞ ሕዝቡ ነው። ዘርፉ የቅርሶችንና መዳረሻዎችን ልማትና እንክብካቤም ይሻል። ለዘርፉ የሚሰጥ ትኩረት ሀገርንም፤ ሕዝብንም ይጠቅማል፤ ጥቅሙ ከዕለት ጉርስ እስከ ጥሪት ይዘልቃል። በዚህ ሂደት ሕዝቡ በየአካባቢው ያሉ ብሔራዊ ፓርኮችን፣ ቅርሶችን እና የቱሪስት መዳረሻዎችን የኔ ብሎ መጠበቅ ይኖርበታል። ለምሳሌ፡- ብሔራዊ ፓርክ ወይም በመዳረሻ ላይ ጉዳት ቢደርስ በቀጥታ ተጎጂው የአካባቢው ነዋሪ ነው። ምክንያቱም ቱሪስት ካልሄደና ገቢ ካልተገኘ ገቢ ይደርቃልና።
የጀጎል አለም አቀፍ ቅርስን የታደገው ሀገራዊ ለውጥ
Apr 4, 2026 572
የስልጣኔ መነሻ የጥበብ መፍለቂያ የሆነችው የምስራቋ ፈርጥ ሀረር የንግድ፣ የፖለቲካና ማህበራዊ ትስስር ማዕከል ሆና በትውልድ ቅብብሎሽ ከአንድ ሺህ አመታት በላይ የተሻገረች እድሜ ጠገብ ከተማ ነች። በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በምስራቅ አፍሪካ የእስልምና ሀይማኖት ትምህርትና የንግድ ማዕከል የነበረችው ከተማዋ በርካታ ቋሚና ተንቀሳቃሽ እንዲሁም የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቁሳዊና ሀይማኖታዊ ቅርሶችን የያዘች ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ ነች። ከእነዚህ ቅርሶች መካከል ጥንታዊ የስነ-ህንፃ የጥበብ፣ የከተማ ፕላን፣ ባህላዊ የመሬት አጠቃቀም፤ አካባቢያዊ መስተጋብርና የስልጠኔ መገለጫ በሚል እኤአ በ2006 በተባበሩት መንግስታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ተቋም ዩኔስኮ በአለም አቀፍ ቅርስነት የተመዘገበው የጀጎል ቅርስ ይጠቀሳል፡፡   ቅርሱ ምንም እንኳን በኪነ ህንፃ ጥበብ በላቁ በአርቆ አሳቢ አባቶች እንዳይፈርስና ሚዛኑን ጠብቆ ለረጅም ጊዜ እንዲቆይ በተመረጠ ድንጋይ እና አፈር በልዩ ጥበብ የተገነባ ቢሆንም በጥበቃና እንክብካቤ ጉድለት ምክንያት ከግማሽ ምዕተ አመታት በላይ እድሜን ባስቆጠረው ቅርስ ላይ አደጋ ተጋርጦበት ቆይቷል። በቅርሱ ውስጣዊ እና ውጫዊ ክፍሎች የህገ-ወጥ ግንባታዎች መበራከትና በሌሎች ምክንያቶች በደረሰበት ጉዳት የጥንት ስልጣኔ ምልክት የሆነው አለም አቀፉ የጀጎል ቅርስ ከዩኔስኮ የአለም ቅርስነት እስከመሰረዝ የደረሰ አደጋ ተደቅኖበት ነበር። ሆኖም ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በአዲስ እሳቤ፤ በተደመረ አቅምና በላቀ ቁርጠኝነት፤ ህዝብን በማሳተፍ ከመንግስት ምንም አይነት በጀት ሳይመደብለት ከ25 ኪሎ ሜትር በላይ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች ማልማት ተቻለ። አሁን ላይ እነኛ በሸራና በጨርቅ በተሰሩ ህገወጥ ግንባታዎች ተወሮ የነበረው 3ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው የጀጎል ግንብ ዙሪያ በአበቦችና ቅርሱን በሚያስውቡ ስራዎች ደምቀዋል።   በዚህም አባቶች ከዘመኑ ቀድመው ዛሬም ድረስ ግርምትን በሚያጭር ጥበብ አንፀው ያኖሩት ይህንን የሀገር ሀብት በመታደግ ትውልዱን ከታሪክ ተወቃሽነት ወደ ዳግም ታሪክ ሰሪነት እንዲሸጋገር ማድረግ ተችሏል። ስራውም የትላንትን መሰረት ሳያናጋ፤ የቀድሞ አባቶችን ጥበብና ስልጣኔ ሳይጋፋና ሳይዘነጋ ጥንታዊውን ከዘመናዊ ጋር አዋህዶ ቅርስ መገኛ ለሆኑ ሌሎች አካባቢዎችም ተምሳሌት በሚሆን ደረጃ አስደናቂ ስራ ተከናወነ። የአካባቢውን ሀብትና እውቀት በመጠቀም እውን የተደረገው ይህ ስራ በእያንዳንዱ የሀረሪ ጥንታዊ ቤቶች በሚገኙ የታሪክ አሻራዎችና የባህል መገለጫዎች እንዲደምቅም ሆኗል። ይህ ትውልድ ተሻጋሪ ስራ ቅርሱን ከአደጋ ከመታደግ ባለፈ ከገጠር እስከ ከተማ፣ ከግለሰብ እስከ ማህበራትና የዳያስፖራ አባላት ድረስ ሁሉም በያገባኛል ስሜት አሻራውን ያኖረበት ዘመን ተሻጋሪ ፕሮጀክት ነው። ይህም በቅርሱ ላይ የእኔነት ስሜት እንዲጎለብት በማድረግ የእይታ ለውጥ እንዲመጣ ያስቻለና ቀደም ሲል የነበሩ የግለኝነት አስተሳሰቦችን በመቅረፍ የወል እሳቤ እውን የሆነበት ፕሮጀክት ሆኖ ታይቷል።   ዛሬ ላይ እነኛ የቆሻሻ መጣያ የነበሩ እና በአካባቢው ለማለፍ ከባድ የነበሩ የጀጎል መንገዶች ፀድተው ውብ ሆነዋል። ይዘታቸውን ለቀው የነበሩ ቅርሶችም የአለም ቅርስነት ክብርና መስፈርትን በሚመጥን ደረጃ ታድሰዋል። ዛሬ የጀጎል ነዋሪ እንደቀድሞ አካባቢውን ለቆ ለመሄድ ሳይሆን መኖርን የሚመርጥባት የወጣውም መመለስን የሚመኝባት ምቹ አካባቢ ሆናለች። የመቻል ምልክት የትብብር ውጤትና የአብሮነት ጉልበት በተግባር የታየበት የጁገል መልሶ ልማት ጥንታውን መንደር ለነዋሪዎች ምቹ ለጎብኚዎች ተመራጭ የጉብኝት ስፍራ እንዲሆን ማድረግ ተችሏል። በለውጡ መንግስት በአዲስ መልክና ቀለም የተዋበው ጀጎል የሀረርን ቀደምት ስልጣኔ እየመሰከረ የሀገርንም ገፅታ እየገነባ ይገኛል።
የለውጡ ትሩፋት - ግብርናን የሚያሻግረው ዕይታ
Apr 3, 2026 382
የለውጡ ትሩፋት - ግብርናን የሚያሻግረው ዕይታ በአሸናፊ በድዬ በኢትዮጵያ መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም ልዩ ቀን ሆኖ በታሪክ ተመዝግቧል። ዕለቱ አዲስ ምዕራፍ የተከፈተበትና ታሪካዊ የለውጥ ጉዞ የተጀመረበት ነው። ኢትዮጵያ ከለውጡ በኋላ በፖለቲካ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች መሠረታዊ ውጤቶችን እያስመዘገበችም ትገኛለች። በተለይ በሀገር አቀፍ የኢኮኖሚ ሪፎርም መሰረት ፈጣን፣ አስተማማኝና ዘላቂነት ያለው ኢኮኖሚ ዕድገት ለማስመዝገብ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል። ለዚህም ነው ዕድገቱን ፈጣንና ተከታታይ ለማድረግ አምስት ዋና ዋና የኢኮኖሚ ምሰሶዎች ተለይተው ወደ ሥራ የተገባው። እነዚህ ዘርፎች ኢኮኖሚው በአንድ ዘርፍ ላይ ብቻ ተንጠልጥሎ እንዳይቀርና በማንኛውም ዓለም አቀፋዊ ጫና ውስጥ የማይናወጥ ጽኑ መሠረት እንዲኖረው ያደርጋል። በተለይም ግብርናው ለኢንዱስትሪው ግብዓት ሲያቀርብ፣ ቴክኖሎጂው ደግሞ የግብርናውን ምርታማነት ሲያሳልጥ፣ ማዕድንና ቱሪዝም ደግሞ ለሌሎች ዘርፎች መስፋፋት ወሳኝ የሆነውን የውጭ ምንዛሬ ሲያመነጭ የተቀናጀ የሰንሰለት አሰራር መዘርጋት ይችላል። በዚህ መሠረት፣ ከለወጡ ወዲህ የሀገሪቷን የኢኮኖሚ ገጽታ እየቀየሩ ያሉትን እነዚህን ዘርፎችና የታሪካዊ ቀኗን ትሩፋት በወፍ በረር እንመለከታለን። 1. ግብርና ፦ የስንዴ አብዮት ግብርናው አሁንም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ነው። ከለውጥ ማግስት በኋላ ከዝናብ ጥገኝነት በመውጣትና በቴክኖሎጂ በመታገዝ በዘርፉ ታሪክ ቀያሪ ስኬት እየተመዘገበ ይገኛል። የዚህ ስኬት ዋነኛ ማሳያ ደግሞ በዓለም አቀፍ ደረጃ አድናቆትን ያተረፈው የኢትዮጵያ የስንዴ አብዮት ነው። 👉የቀድሞ ቅኝት፦ የዳራ እውነታዎችና የጥገኝነት ቀንበር ከሀገራዊ ለውጡ በፊት የኢትዮጵያ ግብርና ገጽታ በእድገት ማነቆዎች የተጠፈረ ነበር። ኢትዮጵያ ሰፊ ለም መሬት፣ አመቺ የአየር ንብረትና ብዙ የሰው ኃይል እያላት ለዓመታዊ የፍጆታ ፍላጎቷ የሚሆን በቂ ስንዴ ማምረት አቅቷት ለዓመታት ቆይታለች። በዚህም ምክንያት በየዓመቱ ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ በሚደርስ የውጭ ምንዛሬ ስንዴ በመግዛት ከውጭ ለማስገባት ትገደድ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ታሪኳ ነው። የዚህ ዓይነቱ አካሄድ ኢትዮጵያ የማምረት አቅም እያላት ለውጪ ምንዛሪ ወጪ ዳርጓት ቆይቷል፤ በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ የሚፈጠሩ የዋጋ መዋዠቆችና ጂኦ-ፖለቲካዊ ቀውሶች ተጋለጭነቷን አስፍቶት እንደነበር የሚታይ እውነት ነው። 👉የለውጡ ስትራቴጂና ቁርጠኝነት የስኬት ጅማሮ ይህ ቢያንስ በስንዴ ጥገኛ አድርጎን የቆየው ተግዳሮት ታሪክ በሚቀይር መልኩ አዲስ ምዕራፍ ያስከፈተው መጋቢት 24 ቀን 2018 ዓ.ም የተጀመረው ሀገራዊ ለውጥ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነትና ያላሰለሰ ክትትል የተጀመረው የተቀናጀ ጥረት የኢትዮጵያን ግብርና ከነበረበት ተግዳሮት አላቆ ዘመናዊና ውጤታማ ምዕራፍ ያሸጋገረው ጉዞ ጀምሯል። ለዚህ በአብነት የሚጠቀሰው የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ስትራቴጂ ነው። በ2011 ዓ.ም በሙከራ ደረጃ በ3 ሺህ 500 ሄክታር መሬት ላይ ብቻ የተጀመረው የመስኖ ስንዴ ልማት፣ ዘንድሮ አራት ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ሄክታር ደርሷል፡፡ የምርት መጠኑም ከ100 ሺህ ኩንታል ወደ 175 ሚሊዮን ኩንታል ከፍ ብሏል፡፡ በአሁኑ ወቅት በመኸር፣ በበልግና በመስኖ የሚለማው መሬት ስፋት ከሀገራዊ ለውጡ በፊት ካለው ጋር ሲነጻጸር እምርታዊ ለውጥ ማሳየቱን ማስተዋል ይቻላል። በዚህም ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀዳሚ ስንዴ አምራች ሆናለች። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ባሳለፍነው ዓመት ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በኢኮኖሚው ዘርፍ ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ኢትዮጵያ በአፍሪካ አንደኛ ስንዴ አምራች ሀገር መሆኗን መግለጻቸውን ይታወሳል። ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ የጀመረችው ስትራቴጂያዊ ንቅናቄ በሀገሪቷ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ የምርት ዕድገት አስመዝግቧል። ይህም የዘርፉን ጉዞ ከነበረበት ዝቅተኛ ደረጃ አላቆ በአጭር ጊዜ ውስጥ በብዙ እጥፍ እንዲልቅና ለሀገራዊ የምግብ ሉዓላዊነት ዋነኛ መሰረት እንዲሆን አስችሎታል። 👉የምግብ ሉዓላዊነትና የሀገር ክብር ዛሬ ኢትዮጵያ ስንዴን ከውጭ ከማስገባት መላቀቅ ብቻ ሳይሆን፣ ስንዴ ለውጭ ገበያ መላክ የጀመረችበት አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ላይ ትገኛለች። ይህም የለወጡ ትሩፋት ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬን በማዳን፣ በዓለም አቀፍ መድረክ የኢትዮጵያን ተደራዳሪነትና ክብር ከፍ አድርጓል። በተጨማሪም እንደ አረንጓዴ አሻራ፣ የሌማት ትሩፋትና መሰል መርሃ-ግብሮች በዘርፉ እምርታዊ ለውጥ እያመጡ ይገኛሉ። 2. ኢንዱስትሪ የኢንዱስትሪው ዘርፍ በተለይም አምራች ኢንዱስትሪው ከመጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም ወዲህ የሀገር ውስጥ ምርትን በመተካትና ለውጭ ገበያ የሚሆን ጥራት ያለው ምርት በማቅረብ ላይ ያተኮረ ነው። በ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ አማካኝነት ከዚህ ቀደም ተዘግተው የነበሩ በርካታ ፋብሪካዎች ወደ ሥራ ተመልሰዋል። የኮንስትራክሽን ግብዓቶችን (እንደ ሲሚንቶና ብረት) በሀገር ውስጥ የማምረት አቅም በማደጉ የግንባታ ዘርፉን አነቃቅቷል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመነትን በመሳብ ለሺዎች የሥራ ዕድል ፈጥረዋል። 3. ማዕድን ኢትዮጵያ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት በሳይንሳዊ መንገድ በመጠቀም የውጭ ምንዛሬ ግኝቷን ለማሳደግ ከለውጡ ወዲህ ትልቅ ርብርብ እየተደረገ ነው። የወርቅ፣ የድንጋይ ከሰልና የሌሎች ማዕድናት ምርት በከፍተኛ ሁኔታ አድጓል። በተለይ የድንጋይ ከሰልን በሀገር ውስጥ ማምረት መቻሉ ለሲሚንቶ ፋብሪካዎች የሚወጣውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ቀንሷል። በዘርፉ ሕገ-ወጥ ዝውውርን በመቆጣጠርና ዘመናዊ አሰራርን በመዘርጋት የመንግሥት ገቢ እንዲያድግ ተደርጓል። 4. ቱሪዝም ከመጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም ወዲህ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመጪነትና ተግባራዊ ስራዎች ቱሪዝም በአዲስ መልክ የተወለደና ትልቅ ተስፋ የተጣለበት ዘርፍ ሆኗል። ቀደም ሲል በታሪካዊና ተፈጥሯዊ ቅርሶች ላይ ብቻ ተወስኖ የቆየው እንቅስቃሴ፣ አሁን ላይ ሰው ሰራሽ መስህቦችን በማካተት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቱን አረጋግጧል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተገነቡት አንድነት፣ እንጦጦና ወዳጅነት ፓርኮች የአዲስ አበባን ገጽታ ሙሉ በሙሉ ከመቀየራቸውም በላይ ለከተማ ቱሪዝም አዲስ ምዕራፍ ከፍተዋል። በ"ገበታ ለሀገር" መርሃ-ግብር የተገነቡትና በቅርቡ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት የሆኑት እንደ ወንጪ (Eco-Tourism)፣ ጎርጎራ ያሉ መዳረሻዎች የሀገሪቷን የቱሪዝም ሀብት ወደ ክልሎች በማስፋፋት ረገድ ትልቅ ስኬት አስመዝግበዋል። በቅርቡ ተመርቆ ወደ ሥራ የገባው የታላቁ ቤተ-መንግሥት የቱሪስት መዳረሻ እና በ"ገበታ ለትውልድ" ስር እየተገነቡ ያሉ ፕሮጀክቶች ዘርፉን ይበልጥ አጠናክረውታል። አዲስ አበባ የአፍሪካ መዲና በመሆኗ፣ በትላልቅ ስብሰባዎች አማካኝነት የሚገኘው ገቢ በከፍተኛ ሁኔታ አድጓል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 2ኛ መደበኛ ጉባዔ ላይ የከተማ አስተዳደሩን የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ያስታወቁት፤ አዲስ አበባን የቱሪዝም ኮንፍረንስ ማዕከል ለማድረግ የተከናወኑ በርካታ የልማት ሥራዎችና ሜጋ ፕሮጀክቶች ፍሬ ማፍራት በመጀመራቸው፣ በከተማዋ የሚካሄዱ ኩነቶች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን ነው። በዚህም ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ ብቻ 150 የሚሆኑ አህጉር አቀፍና ዓለም አቀፍ ኹነቶች በአዲስ አበባ የተካሄዱ ሲሆን፤ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ50 በመቶ ዕድገት ማሳየቱን መግለጻቸው ይታወቃል። ከሀገር ውስጥና ከውጭ ሀገር የቱሪስት ፍሰት ጋር ተያይዞ ባለፉት ስድስት ወራት 155 ቢሊየን ብር ወደ ኢኮኖሚው ፈሰስ መደረጉን የገለጹ ሲሆን፤ መዲናዋን የቱሪዝም ኮንፍረንስ ማዕከል ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ለኹነቶቹ መጨመር በተጨባጭ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ናቸው ብለዋል። የአዲስ አበባ ከተማን ጨምሮ በክልሎች ከተሞች እየተሰሩ ያሉት የኮሪደር ልማቶች ከተማዎቹን ልዩና ውብ ከማድረጋቸው ባሻገር ለቱሪስት መስህብ ሆነዋል። 5. ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ/ዲጂታል ኢኮኖሚ ይህ ዘርፍ የኢኮኖሚ ምሰሶዎችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በመደገፍ ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ የሚያደርግ ከመጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም ለውጥ ወዲህ የደመቀ የለውጥ ሞተር ነው። የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2025" ስኬቶች በርካታ የመንግሥት አገልግሎቶች (ፓስፖርት፣ ንግድ ፈቃድና ታክስ ክፍያ) በበይነ-መረብ በመሆናቸው ሌብነትንና እንግልትን ይቀንሳሉ። በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች በ"ፋይዳ" መታወቂያ የታቀፉ ሲሆን፤ በ"ቴሌ ብር"ና መሰል አማራጮች የገንዘብ ዝውውር መዘመን ችሏል። የሳፋሪኮም ኢትዮጵያ ወደ ሥራ መግባት የአገልግሎት ጥራትንና ተደራሽነትን ጨምሯል። የ"ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030" ራዕይ የ2025 ስኬትን መሠረት በማድረግ አሁን ላይ አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን (AI) በስፋት የመጠቀም ግብ ወዳለው ቀጣይ ምዕራፍ ተሸጋግሯል። በ"ኢትዮ-ኮደሮች" መርሃ-ግብር አምስት ሚሊዮን ወጣቶችን በዲጂታል ክህሎት ለማሰልጠን እየተሠራ ያለው ሥራ ወጣቶችን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እያደረገም ይገኛል። እነዚህ አምስት ምሰሶዎች ተነጣጥለው የሚታዩ ሳይሆን አንዱ ሌላውን የሚደግፉ ናቸው። ይህ ታሪካዊ ለውጥ ኢትዮጵያን ወደ ብልጽግና ማማ የሚያሸጋግር ስትራቴጂ ነው። የነገዋ ኢትዮጵያ በራሷ የምትመገብና ለሌሎችም የምትተርፍ ጠንካራ ሀገር መሆኗን ያረጋገጠ ታርካዊ ክንውን ነው።
ከመጋቢት ሥጦታዎች መካከል - የጉባ ብሥራቶች  
Apr 2, 2026 3263
በዮሐንስ ደርበው የብርቱዎቹ ልጆች ብርታት በቀጣይ ...! ተከፍሎ የማያልቅ የኢትዮጵያ እና ሕዝቧ ውለታ አለብን - የመናዊያን ፍልሰተኞች ሥልጣኔ - በምርጫ ካርድ መሪን መምረጥ! መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም በኢትዮጵያ የለውጥ ብሥራት ከጫፍ እስከ ጫፍ የተሰማበት ነው። በለውጡ የስምንት ዓመታት ፈጣን ጉዞ በየዘርፉ ይበል የሚያሰኙ አመርቂ ሥራዎች ተከናውነዋል፤ ስኬቶች ተመዝግበዋል። በስምንት ዓመት ጉዞ ውስጥ ከስኬት ወደ ስኬት በመሻገር በርካታ ተግባራት ተሠርተዋል። የሀገሪቷን ቀጣይና ዘላቂ እድገት የሚያተልሙ፣ ሕዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ውጤታማ ተግባራት የተከናወነባቸው ስምንት ዓመታት አልፈዋል። ሌሎች ሜጋ ፕሮጀክቶችን ለማስጀመር ቃል በመግባት የተግባር እርምጃ ተጀምሯል። • የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ መመረቅን ተከትሎ ይፋ የተደረጉ ሜጋ ፕሮጀክቶች - የጉባ ብሥራቶች ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተመርቋል። በዚሁ ወቅት ለመላው ኢትዮጵያውያንና ለኢትዮጵያ ወዳጆች እንኳን ደስ አላችሁ፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለጥቁር ሕዝቦች ሁሉ ታሪክ ሆኖ የሚቀጥል ገድል ነው ብለዋል። የግድቡ ግንባታ ተጠናቆ ኢትዮጵያ ወደ ሌላ ምዕራፍ እንደምትሸጋገር አብሥረዋል። በቀጣይ የሚገነቡ ሜጋ ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶችንም ጉባ ላይ ይፋ አድርገዋል። ለፕሮጀክቶቹ ከ30 ቢሊየን ዶላር በላይ ወጪ ይደረጋል። እነዚህ ፕሮጀክቶችም፤ የኒውክሌር ኃይል ማመንጫ፣ የጋዝ ፋብሪካ ማስመረቅ፣ የነዳጅ ማጣሪያ ግንባታ፣ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ ሁለተኛው የጋዝ ፋብሪካ ግንባታ፣ የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ እና ከ1 ነጥብ 5 ሚሊየን በላይ ቤቶችን መገንባት የሚሉት ናቸው። እነዚህ የለውጡ መንግሥት ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ስትራቴጂያዊ ፕሮጀክቶችን ነድፋ እየሠራች መሆኗን ያረጋግጣሉ። ለዚህም ማሳያ የጉባ ብሥራቶች በታቀደላቸው የጊዜ ገደብ ሲጠናቀቁ ኢትዮጵያ በቀጣናው ያላትን የኢኮኖሚ ዐቅም ያጠናክራሉ። • ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያኔ ካበሠሯቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች መካከል አብዛኞቹ ወደ ትግበራ ምዕራፍ ተሸጋግረዋል። ወር ባልሞላ ጊዜም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) መስከረም 22 ቀን 2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ከዳንጎቴ ግሩፕ ጋር በመተባበር የሚገነባውን የዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካ የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል። በዚሁ ወቅትም የማዳበሪያ ፋብሪካው በዓመት 3 ሚሊየን ቶን ማዳበሪያ አምርቶ ያቀርባል ማለታቸው ይታወሳል። ሕዳር 29 ቀን 2018 ዓ.ም ደግሞ የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ልማት መርሐ-ግብር ማስጀመሪያና የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኃይል ኮሚሽን ሥራ ማስጀመሪያ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። የኢትዮጵያ የኒውክሌር ኢነርጂ ኮሚሽነር ሳንዶካን ደበበ በወቅቱ፤ የኢትዮጵያ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ልማት የኃይል ደኅንነትን በማረጋገጥ ኢኮኖሚያዊ ሽግግርና የረጅም ጊዜ የመቋቋም ዐቅም ግንባታ ላይ የተመሠረተ ብሔራዊ የልማት ተነሳሽነት ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ሰላማዊ የኒውክሌር ቴክኖሎጂ ንጹህ የኃይል አቅርቦት የማመንጨት ዐቅምን በማላቅ በጤና፣ ግብርና፣ በኢንዱስትሪ እና የምርምር ትግበራ ማዕቀፍ የተቃኘ መሆኑንም ነው ያብራሩት። በተመሳሳይ መስከረም 22 ቀን 2018 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) በሶማሌ ክልል ካሉብ በዓመት 111 ሚሊየን ሊትር ማምረት የሚችለውን የኦጋዴን ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ ፕሮጀክት የመጀመሪያ ዙር መርቀዋል። ከዚሁ ጎን ለጎን የጎዴ ነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካ ግንባታ የመሠረት ድንጋይም አስቀምጠዋል። የጎዴ ነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካ ግንባታ ሲጠናቀቅ፤ የኢትዮጵያን የናፍጣ እና የቤንዚን ፍላጎት ከ80 እስከ 90 በመቶ የመሸፈን ዐቅም እንዳለው በዚሁ ወቅት የማዕድን ሚኒስትር ሀብታሙ ተገኝ (ኢ/ር) መናገራቸው ይታወሳል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ሥራን ጥር 2 ቀን 2018 ዓ.ም የመሠረት ድንጋይ በማስቀመጥ አስጀምረዋል። በወቅቱም፤ አውሮፕላን ማረፊያው በአፍሪካ ታሪክ ትልቁ የአየር ትራንስፖርት መሠረተ-ልማት ፕሮጀክት እንደሚሆን ተመልክቷል። ይህም ከኢትዮጵያ ሀገራዊ የኢኮኖሚ ሪፎርም፣ የኢንዱስትሪ ማስፋፊያ አጀንዳ እና የረጅም ዘመን የአቪዬሽን ስትራቴጂ ጋር የተናበበ መሆኑን አስገንዝበዋል። ግንባታው ሲጠናቀቅም አፍሪካን ከዓለም ቀዳሚ የአየር ትራንስፖርት መናኸሪያዎች አንዷ የሚያደርጋትን በዓመት 110 ሚሊየን መንገደኞችን የማስተናገድ ዐቅም ይኖረዋል። ከወትሮው በተለየ በጾም ወቅት እንዲዘወተሩ የሚመከሩ ምግቦች አሉ? ባሳለፍነው ሳምንት ... የመልከ መልካሟ ብዙ መልኮች   • በአጠቃላይ የጉባ ብሥራቶች የኢትዮጵያን ዕድገት በማሳለጥ ሂደት የጎላ ድርሻ አላቸው። ፕሮጀክቶቹ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቁ፣ በሥራ ዕድል ፈጠራ ብሎም በኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ ሚና ያበረክታሉ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት እንድትሆንም ያስችላሉ። እነዚህ ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያ በኃይል አቅርቦት ያላትን ዐቅም በማሳደግ፤ ኢንቨስትመንት በመሳብ እና የውጭ ምንዛሪን በማሳደግ፣ መሠረተ-ልማቶችን በማስፋፋት ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንደሚኖራቸው ይታመናል። ከለውጡ ወዲህ ኢትዮጵያ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ጀምራ የመጨረስ ዐቅሟ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መሆኑን እያየን ነው። በቀጣይም የጀመረቻቸውን ሜጋ ፕሮጀክቶች ባሰበችው ጊዜ እንደምታጠናቅቅ እሙን ነው።
የሀገራዊ ለውጡ አዲስ ምዕራፍ - የሌማት ትሩፋት
Apr 1, 2026 840
ሀገራዊ ለውጡ ከመጣ ከመጋቢት 24/2010 በኋላ ትኩረት ከተሰጣቸውና ተተግብረው ስኬታማ ከሆኑት የልማት ኢኒሼቲቮች መካከል አንዱ የሌማት ትሩፋት ነው። የሌማት ትሩፋት በዋናነት የከተማና የገጠር አርሶ አደሮችን በማቀናጀት፣ በአነስተኛ ቦታ ላይ ሁሉ የጓሮ አትክልትና የዶሮ እርባታን በማስፋፋት በርካታ ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረገ ፕሮግራም ነው። የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚያግዙ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን ማለትም ወተት፣ ሥጋ፣ አሳ፣ እንቁላልና ማርን እንዲሁም አትክልትና ፍራፍሬን በስፋት በማምረት የሥርዓተ-ምግብ ማሻሻልን ዓላማ በማድረግ እየተተገበረ ያለ ሀገራዊ ኢኒሼቲቭ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሌማት ትሩፋትን በጥቅምት ወር 2015 ዓ.ም በአርባምንጭ ከተማ በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት በምግብ ራስን አለመቻል የሀገርን ክብር ይነካል፣ ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ካልቻለች ሙሉ ነፃነት ሊኖራት አይችልም ማለታቸው ይታወሳል። በስንዴ ምርት የታየው ስኬት ወደ እንስሳት ሀብት ልማት (ወተት፣ እንቁላል፣ ስጋና ማር) መደገም እንዳለበትም አሳስበው ጤናማና አምራች ትውልድ ለመፍጠር ሌማታችንን በተመጣጠነ ምግብ መሙላት አለብን በማለት ማስገንዘባቸውም እንዲሁ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በቂ እና አመርቂ ምግብ ማግኘት መሆኑን በመጠቆም በቂ የመጠን፣ አመርቂ ደግሞ የይዘት ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። የሌማት ትሩፋት ግብ በቤተሰብ ደረጃ የተመጣጠነ ምግብን ተደራሽ በማድረግ የህፃናት መቀንጨርን መቀነስ፣ ለወጣቶችና ለሴቶች ሰፊ የሥራ ዕድል መፍጠር፣ እንዲሁም ከሀገር ውስጥ ፍጆታ የተረፈውን ምርት ለውጭ ገበያ በማቅረብ የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ግኝት ማሳደግና የዜጎችን የኑሮ ደረጃ በዘላቂነት ማሻሻል መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ይህ ሀገራዊ ኢኒሼቲቭ የተለያዩ የትኩረት መስኮች አሉት። የላሞችን ዝርያ ማሻሻልና የወተት ምርትን ማሳደግ፣ የእንቁላልና የዶሮ ሥጋ ምርትን በየቤተሰቡ ተደራሽ ማድረግ፣ ዘመናዊ ቀፎዎችን በመጠቀም የማር ምርትን በጥራትና በብዛት መጨመር እንዲሁም ጥራት ያለው የስጋ ምርት ማቅረብ ቁልፍ ምሰሶዎች ናቸው። ግብርናና የእንስሳት እርባታን የከተማ ግብርና አካል የማድረግ ሰፊ ንቅናቄ መፈጠሩ ከታዩ ለውጦች መካከል የሚጠቀስ ነው። የዶሮና የእንቁላል ምርት በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል። በብዙ ክልሎች የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎችና የምርት መሰብሰቢያ እና ማከማቻ ማዕከላት ተስፋፍተዋል። የሌማት ትሩፋት ለወጣቶችና ለሴቶች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር የገቢ ምንጭ ሆኗል። ከመደበኛው የሰብል ምርት በተጓዳኝ አርሶ አደሩ በየቀኑ ገቢ ማግኘት መቻሉ የኑሮ ደረጃው እንዲሻሻል በእጅጉ አግዟል። በፕሮቲን የበለፀጉ ምግቦችን ለህጻናትና ለነፍሰ ጡር እናቶች ተደራሽ በማድረግ በኩል ለውጥ መታየቱን የግብርና ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። በሀገር አቀፍ ደረጃ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የአንድ ቀን ጫጩቶች፣ የተሻሻሉ የወተት ላሞችና ዘመናዊ የንብ ቀፎዎች ለአርሶ አደሩና ለከተማ ነዋሪው ተደራሽ መደረጋቸው፣ ቀደም ሲል በግዢ ብቻ ይሟሉ የነበሩ የእንቁላል፣ የወተትና የማር ምርቶች አሁን ላይ በብዙ ቤተሰቦች ጓሮ እንዲመረቱ አድርጓል። ይህ ተሞክሮ በቤተሰብ ደረጃ የፕሮቲን አቅርቦትን በማሳደግ በሕፃናት ላይ የሚታየውን የምግብ እጥረትና መቀጨጭ ለመቀነስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ሲሆን በተለይም የከተማ ግብርናን በማስፋት ነዋሪው በውስን ቦታ ምርታማ መሆን እንደሚችል በተግባር የታየበት እንደመሆኑ በምግብ ራስን የመቻል ጉዞ ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ታይተዋል። በተጨማሪም፣ ጥራት ያለው የማርና የሥጋ ምርት ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የተጀመሩ ጥረቶች የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ግኝት ለማሳደግ አዲስ በር ከፍተዋል። የሌማት ትሩፋት ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ለመቻልና የዜጎቿን የአመጋገብ ሥርዓት ለማሻሻል የጀመረችው ስትራቴጂካዊ ጉዞ አካል ሲሆን፣ ከመነሻው አንስቶ በምርት ዕድገት፣ በሥራ ዕድል ፈጠራና በሥራ ባህል ለውጥ ረገድ ተስፋ ሰጪ ውጤቶችን አሳይቷል። ይህ ንቅናቄ በተለይ የእንስሳት ተዋጽኦን በየጓሮውና በየቤቱ ተደራሽ በማድረግ በሕፃናት ላይ የሚታየውን የመቀንጨር እና የመቀጨጭ ችግር ለመቅረፍና አነስተኛ አምራቾችን የዕለት ገቢ ባለቤት ማድረግ አስችሏል። የሌማት ትሩፋት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የሥነ ምግብ ሚዛን መዛባትን ለማስተካከል አርሶ እና አርብቶ አደሩም ይሁን የከተማ ነዋሪው በአካባቢው ያሉ አቅሞችን ሁሉ ወደ ልማት በመቀየር ሌማቱን ከመሙላት ባሻገር ለሌሎች ለመትረፍ የሚተጉበት ሀገራዊ ለውጡ ያስገኘወ ስኬታማ የንቅናቄ ፕሮግራም ነው፡፡ በአጠቃላይ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለዘላቂ ብልጽግና መሠረት የሚጥል ታላቅ ብሔራዊ ፕሮግራመ መሆኑን በተጨባጭ እያረጋገጠ ነው።
በኢዜአ ዐይን …!  
Mar 29, 2026 4343
በዮሐንስ ደርበው ሥልጣኔ - በምርጫ ካርድ መምረጥ በያዝነው ዓመት ወርኃ ግንቦት በባተ 24ኛው ቀን ኢትዮጵያ 7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ ለማካሄድ ቀን ቆርጣለች። ለዚህም ቅድመ ዝግጅቶችን በማጠናቀቅና የጊዜ ሰሌዳ በማውጣት ወደ ትግበራ ምዕራፍ ገብታለች። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምርጫውን ተዓማኒ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውን፤ ቀሪ ሥራዎችም እየተከናወኑ መሆኑን ገልጿል። ለዚህም የምርጫ ሕጉን ከማሻሻል ጀምሮ በቴክኖሎጂ የታገዙ ሥርዓቶች ወደ ሥራ መግባታቸው በአሥረጂነት ይጠቀሳሉ። በተጨማሪም የምርጫ ትምህርትና ግንዛቤን ለማስፋት ለሚሠሩ በርካታ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ፈቃድ መሰጠቱ፤የምርጫ ሂደትን ፍትሐዊነት ለማረጋገጥም በርካታ የሀገር ውስጥ ድርጅቶች በኦንላይን ሥርዓት በታዛቢነት መመዝገባቸውን አስረድቷል። በኢዜአ ዐይን …! በገበታ ለሀገር የተገለጠው የተደመረ ዐቅም - ለኢትዮጵያ ስኬቶች እንደማሳያ የጤና ነገር … እንዲሁም ዐለም ዐቀፍ ታዛቢዎች በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አማካኝነት መጥተው ፈቃድ የሚወስዱበት ዝግጅት እየተደረገ ነው። ምርጫ ቦርድ ለመራጮች ምዝገባ አወዳድሮና ገለልተኝነታቸውን በፖለቲካ ፓርቲዎች አስተችቶ ያሠለጠናቸውን 187 ሺህ 28 የምርጫ አስፈጻሚዎች አሠማርቷል። ለመራጮች ምዝገባ የተዘጋጁ 46 ሺህ 757 ጣቢያዎች እና ተጨማሪ በርካታ ንዑስ ጣቢያዎችም ተሠናድተዋል። እንደ ምርጫ ቦርድ መረጃ፤ 46 የፖለቲካ ፓርቲዎች በዘንድሮው ምርጫ ለውድድር ተመዝግበዋል። በሌላ በኩል ደግሞ 73 ዕጩዎች በግል ለውድድር መቅረባቸው ተገልጿል። ምርጫ ነፃ፣ ሰላማዊና ፍትሐዊ ሆኖ የሚከናወነው ሁሉም ፓርቲ ሕግን አክብሮ ኃላፊነቱን ሲወጣ እንደሆነ ያስማማል። የምርጫው ስኬት የሚረጋገጠውም ቦርዱ ለብቻው በሚያደርገው ጥረት ሳይሆን፤ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ዕኩል ኃላፊነቱን መወጣት ሲችል መሆኑ ይታመናል። በመሆኑም በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚወዳደሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሰባት ምዕራፎችና በ30 አንቀጾች የቀረበውን የምርጫ ሥነ-ምግባር ደንብ ፈርመዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በምርጫ ሂደት የዜጎችን ተሳትፎ ለማበረታታት “ምርጫችን ነው-ሀገር ያለኛ” የተሰኘ የምርጫ ኅብረ-ዝማሬ ማስመረቁ ይታወቃል። በዚሁ ወቅት የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ኃይሉ፤ ኅብረ-ዝማሬው አካታች ተሣትፎን ለማበረታታት መሠናዳቱን አስገንዝበዋል። የልዩ ልዩ ድምጾች ኅብራዊነት ያለውን የጋራ ጥንካሬ በማሳየት በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የዜጎችን ተሳትፎ ማጎልበት የኅብረ-ዝማሬው ዓላማ መሆኑም ተገልጿል። በ6ኛው ጠቅላላ ምርጫም “የሀገር ካስማ” የተሰኘ ኅብረ-ዝማሬ ይፋ መደረጉ ይታወሳል። ከየካቲት 28 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በግንቦት ወር ለሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የመራጮች ምዝገባ እየተከናወነ ነው። እስካሁን ባለው መረጃ ምዝገባው እስከ መጋቢት 28 ቀን 2018 ዓ.ም ይቀጥላል። የመራጮች ምዝገባ እየተከናወነ የሚገኘውም፤ በመደበኛ የመራጮች ምዝገባ (ማኑዋል)፣ ምርጫዬ በተሰኘ የሞባይል መተግበሪያ እና በድረ ገጽ ነው። ከአጠቃላይ የምርጫ ጣቢያዎች መካከል በ17 ሺህ ያህሉ የዲጂታል የመራጮች ምዝገባን ተደራሽ ለማድረግ ሲሠራ መቆየቱን ቦርዱ ማሳወቁ ይታወሳል። በዚህም መሠረት ከየካቲት 28 ቀን 2018 ዓ.ም. እስከ መጋቢት 18 ቀን 2018 ዓ.ም. በማንዋልና በዲጂታል አማራጭ በተከናወነ የመራጮች ምዝገባ ከ28 ሚሊየን 365 ሺህ 310 በላይ መራጮች ተመዝግበዋል። በኢትዮጵያ የምርጫ፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባ እና የምርጫ ሥነ-ምግባር ዐዋጅ ቁጥር 1162/2011 አንቀጽ 37(7) ላይ ቦርዱ በድምፅ መስጫ ወረቀት ላይ የዕጩዎች ምሥልና የመለያ ምልክቶችን አቀማመጥ፣ ቅደም ተከተልና እንዲሁም ተያያዥነት ያላቸው ጉዳዮች ለተወዳዳሪ ፓርቲዎች እና የግል ዕጩዎች ግልጽ በሆነ መንገድ በመመሪያ እንደሚወስን ይደነግጋል። በዚህም መሠረት ምርጫ ቦርድ የፖለቲካ ፓርቲ ዕጩዎች በድምፅ መስጫ ወረቀት ላይ የሚኖራቸውን ቅደም ተከተል ለመወሠን የሚያስችለውን የዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓት ባሳለፍነው መጋቢት 14 ቀን በይፋ አስጀምሯል። የድምፅ መስጫ ወረቀት ኅትመት የሚከናወነው በድምፅ መስጫ ወረቀት ላይ የዕጩዎች ምሥልና የመለያ ምልክት አቀማመጥን የሚወሥነው የዕጣ ማውጣት ሂደት መጠናቀቅን ተከትሎ መሆኑ ይታወቃል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መጋቢት 19 ቀን 2018 ዓ.ም. የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የፖለቲካ ፓርቲዎች ነፃ የዓየር ሠዓት ድልድል የዕጣ አወጣጥ ሥነ-ሥርዓት አካሂዷል። በዚህም መሠረት በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለሚወዳደሩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በ24 ሬዲዮ፣ በ20 ቴሌቪዥን እና በ6 ጋዜጦች በሕዝብና በንግድ ሚዲያዎች ነጻ የዓየር ሠዓት ተድልድሎላቸዋል። የሠዓት ድልድሉ ፖለቲካ ፓርቲዎች ፕሮግራማቸውንና ፖሊሲዎቻቸውን እንዲያስተዋውቁ፣ የግል ዕጩዎችም አማራጭ ሐሳባቻቸውን እንዲያጋሩና የምርጫ ቅስቀሳ እንዲያደርጉ ብሎም ከመራጩ ጋር እንዲተዋወቁ ዕድል የሚሰጥ ነው። ይፋ በተደረገው ነፃ የዓየር ሠዓት የተመዘገቡ 46 የፖለቲካ ፓርቲዎችና የግል ዕጩዎች በኃላፊነት ስሜት እንዲጠቀሙ ይጠበቃል። በአጠቃላይ በምርጫ ካርድ መሪን መምረጥ ከሥልጣኔ ቁንጮዎች አንዱ ሆኖ ይነሳል። የመራጮች ምዝገባ ሂደትም የሕዝቡን ዴሞክራሲያዊ ልምምድ ያጎለብታል። ምርጫ፤ ዜጎች ሕገ-መንግሥታዊ መብታቸውን እንዲጠቀሙ፣ ተቋማዊ አሠራርን እንዲያጠናክሩ ብሎም በካርዳቸው ይሁንታ የሚመራቸውን መምረጫ ቁልፍ ነው። ኢትዮጵያ በወሳኝ የምርጫ ወቅት ላይ ናትና፤ ለስኬታማነቱ ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል። #ምርጫ #ኢዜአ #የኢትዮጵያ_ዜና_አገልግሎት #Ethiopian_News_Agency #የመራጮች_ምዝገባ #በኢዜአ_ዐይን
ተከፍሎ የማያልቅ የኢትዮጵያ እና ሕዝቧ ውለታ አለብን - የመናዊያን ፍልሰተኞች
Mar 19, 2026 3222
በዮሐንስ ደርበው ምድረ ቀደምቷ ሀገር ኢትዮጵያ ለተገፉ፣ ጥላ ከለላ ለሚሹ፣ ለተከዙና ለታረዙ የሀገራት ዜጎች መጠጊያ ናት። የኢትዮጵያን ቸርነትም ከተጠለሉባት እንግዶቿ በላይ ምሥክር የለም። የኢትዮጵያን ደጅ የረገጡ ሁሉ በቆይታቸው ለተደረገላቸው ሁሉ ‘ውለታችንን በምን እንክፈል’ ሲሉ ይደመጣሉ። ከአያሌ ሀገራት በመልከ ብዙ ቀውሶች ሳቢያ ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ሁሉ የቆሰሉ ልባቸው ታክሞ፣ ዕንባቸው ታብሶና ሕይወታቸው ታድሶ ኑራቸውን አደላድለዋል። የብርቱዎቹ ልጆች ብርታት በቀጣይ ...! በዚህም ከአፍሪካም ሆነ ከተቀረው ክፍላተ ዓለም የጦርነትና ግጭት ጥላ ያጠላባቸውና ሰላምን የተጠሙ የቀጣናው ሀገራት ዜጎች ኢትዮጵያን ሲሹ ማየት የተለመደ ነው። የየመን ዜጎች ለዚህ ማሳያ ናቸው። ኢብቲሳም ኻሊድ እና መሰል የመናዊያን ከየመን የእርስ በርስ ግጭት በኋላ የኢትዮጵያን ደጅ ረግጠው ዛሬ ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች የሚተርፍ የተድላ ኑሮ እየኖሩ ነው። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረገችው ኢብቲሳም እንደምትለው፤ በየመን አለመረጋጋት በፈጠረው ጠባሳ እርሷና መሰሎቿ ለፍልሰት ተዳርገዋል። ለዚህ ደግሞ ምርጫቸው ኢትዮጵያ ሆነች። ወደ ኢትዮጵያም መጥተው የሀገሬው ፊት ሳይኮሰኩሳቸው በፍቅር እንደተቀበሏቸው ትናገራለች። በዚህም ዛሬ የመናዊያን ተስፋቸው ለምልሞ፣ ሕይወታቸው ሠምሮ ኢትዮጵያን እንደ እናት ቆጥረው እየኖሩ ስለመሆኑ ትናገራለች። ከ11 ዓመታት በፊት ወደ ኢትዮጵያ የመጣችው ኢብቲሳም፤ በወቅቱ ቀኑ እንደጨለመባት ታወሳለች። ሰው ከቤቱ፣ ከወገኑ…ከሀገሩ ወጥቶ ወዴት ይሄዳል? በወቅቱ የነበረውን ጭንቀት ማየልም ታስታውሳለች። አሁን ግን ስለ ኢትዮጵያ እና ሕዝቧ በጎነት ዐውርታ አትጠግብም። “አሁን ፍልሰተኛ አይደለሁም፤ ያለሁት በሁለተኛዋ ሀገሬ ኢትዮጵያ ነውና” ትላለች። እንዲህ ባለው የረመዳን ወቅት ደግሞ የፍልሰተኞች ሁሉ ሰብሳቢ ናት። “ሁሉም ከእነ ቤተሰቡ ወደ ቤቷ እየመጣ ያፈጥራል። በዚህም በፍልሰት እንደመጡ ሳይሆን ቤተሰባዊነት ይሰማቸዋል። ከየመን፣ ሱዳን፣ ሶማሊያ፣ ኤርትራ፣ አፍጋኒስታን፣ ኮንጎሊዝ (DRC) ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ሁሉ ሰብሰብ ብለው የኢፍጣር መርሐ-ግብርን እንደሚያከናውኑም ታነሳለች። በዚህ ላይ ኢትዮጵያውያን ብርታት ናቸው ትላለች፤ ሁሌም ‘አይዟችሁ፣ በርቱ፣ ነገ ጥሩ ይሆናል’ እያሉ ያበረቱናል፤ ክብርና ፍቅር ይሰጡናል ስትልም ታስረዳለች። የኢትዮጵያንና ሕዝቧን ውለታ እንዴት መክፈል ይቻላል? ኢትዮጵያን ሀገራችን ብለን ነው እየጠራን ያለነው። እንደ እንግዳ እንደ ፍልሰተኛ እራሳችንን አናስብም፤ እንደሀገሬው አንዱ እንጅ፤ የምትለው ኢብቲሳም፤ ኢትዮጵያን እንዴት ብዬ ነው የምገልጻት? እናትን መግለጽ ይቻላል? እናትን መግለጽ ከተቻለ ኢትዮጵያን በዚያ ልክ መግለጽ ይቻል ይሆናል፤ እኔ ግን አይቻለኝም በማለት ትናገራለች። “የዛሬ 11 ዓመት ነው ወደ ኢትዮጵያ የመጣሁት፤ የሰው ፊት አልገረፈኝም፤ ፊቱን ያዞረብኝም የለም። ኢትዮጵያውያን ደግ፣ ቅንና ደስ የምትሉ ሕዝቦች ናችሁ” ስትል ስሜቷን ትገልጻለች። ኢትዮጵያ እንደ ኒውዮርክ እያደገች ነው፤ እኛ ከመጣን በኋላ እንኳን በርካታ ለውጦች ዕያየን ነው ስትልም የኢትዮጵያን የለውጥ ሂደት አንስታለች። ለአብነትም ባለፉት ሁለት ዓመታት ብቻ በርካታ ነገሮች መስተካከላቸውን በመጠቆም፤ ለዚህም የኢትዮጵያን መንግሥት እናመሠግናለን ብላለች። ከፍልሰተኞች ጋር በተያያዘ በርካታ ሕጎች በመሻሻላቸው፤ ዛሬ በራሴ ስም ንግድ ፈቃድ አውጥቼ እየሠራሁ ነው፤ በጨረታዎችም እወዳደራለሁ፤ የበጎ አድራጎት ማኅበር መመሥረትና መምራት ችያለሁ። እነዚህ ሁሉ የኢትዮጵያ መንግሥት ያመጣቸው ለውጦች ናቸው ብላለች። በምድረ ኢትዮጵያ ያለን ሁሉ ለኢትዮጵያ ዕድገት እንተባበር ስትልም ጥሪ አቅርባለች። ህልማችን ከኢትዮጵያውያን ጎን ሆነን ኢትዮጵያን በማሳደግ ጥረት በንቃት መሳተፍ ነው፤ የኢትዮጵያን እና ሕዝቧን ውለታ መመለስ አለብን ስትልም ትናገራለች። በኢብቲሳም ኻሊድ ቤት በተዘጋጀ የኢፍጣር መርሐ-ግብር ላይ የተሳተፈው አነስ አንዋር ለኢዜአ እንዳለው፤ ኢትዮጵያ በሯን ከፍታ አስጠልላዋለች። ከተለያዩ ሀገራት ብንመጣም ሰብሰብ ብለን ስናፈጥር፤ ማኅበራዊና ቤተሰባዊነታችን ይጠናክራል ብሏል። ብዙ ፈተናዎችን ዐይተናል፤ አልፈናቸው እዚህ ደርሰናል የሚለው አነስ፤ “ኢትዮጵያዊነት መልካምነት ነው” ሕዝቡ በክብር ነው የተቀበለን፤ ከምሥጋና ውጭ ምን ማለት እንችላለን? አመሥጋኞች ነን ሲል ገልጿል። እየተማርኩ ነው፤ ትምህርቴን አጠናቅቄ በሙያዬ በመሠማራት ኢትዮጵያን ማገዝ እፈልጋለሁ ብሏል። ራኪያ አሊ አብዱረዛቅ በበኩሏ በፈረንጆቹ 2011 ወደ ኢትዮጵያ መምጣቷን ታወሳለች። ትምህርቷንም ተከታትላ መመረቋን ገልጻ፤ ቤተሰብ አፍርታ ሁለት ልጆችንም ወልዳ እየኖረች ነው። ኢትዮጵያ ሁለተኛ ሀገሬ ናት፤ ሰላም አላት፤ ሕዝቡም ሰው አክባሪ ነው። ለኢትዮጵያ የተሻለ ልማት ደግሞ መተባበር ወሳኝ ስለሆነ ለዚሁ እንትጋ ስትል መልዕክቷን አስተላልፋለች። #ፍልሰተኞች #ኢዜአ
ከዛፍ የሚታለብ ወተት
Feb 27, 2026 1370
በቀደሰ ተክሌ -(ከሚዛን አማን ቅርንጫፍ) ጥበብ ከተፈጥሮ ጋር ስትገናኝ ሌላ እውነት ሌላ አዲስ ነገር ትፈጥራለች። የሰው ልጅ የመመራመርና የማወቅ ተፈጥሯዊ ባህርይው በተፈጥሮ ላይ ሁሉን የማድረግ ሥልጣንን ያስቸረ ነው። ሰው ያልነበረን አዲስ ነገር መፍጠር ባይችልም፤ ከነበረው ሌላ ውጤት ማግኘት ወይም መፍጠር ይችላል። "ጉማታ" በረከትን የመጋራት እሴት!! በዓለማችን ሰውን እና እቃን ከቦታ ወደ ቦታ የማንቀሳቀስ ትልቅ አገልግሎት ያለው ተሽከርካሪ ሕይወት ያለው መስሎ እንዲታይ የሚያደርገው የተገጠመለት ጎማ ነው። ታዲያ ይህ ጎማ ከዛፍ በተገኘ የወተት ጠብታ የሚሰራ መሆኑ አግራሞትን ከሚፈጥሩ የጥበብ ሥራ ውጤቶች መካከል እንዲሆን ያደርገዋል። የጎማ መስሪያ የሆነው ጥሬ ምርት ከዛፍ እንዴት እንደሚዘጋጅ ከስፍራው ኢዜአ የተመለከተውን ሊያስቃኛችሁ እነሆ ይላል፡- በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የጎማ ዛፍ ልማት በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ቤንች ሸኮ ዞን ጉራ ፈርዳ ወረዳ ይገኛል። በምስራቅ አፍሪካ ብቸኛ የተባለው ይህ የጎማ ዛፍ ልማት በ3 ሺህ 884 ሔክታር መሬት ላይ ያረፈ ነው። አረንጓዴ ካባ የደረበውን የበበቃ ቀዬ እንደተሻገሩ ቀጥ ቀጥ ብለው የቆሙ ዛፎች ቅርንጫፋቸውን ከመሬት ከፍ አድርገው ግንዱን ለሌላ ተግባር እየተዉ አድገው በአዲስ ብርሃን ቀበሌ ደምቀው ይታያሉ።   እነዚህ ዛፎች ከወገብ በታች ባለው ክፍል ብዙ ሺህ ጅራፍ እንዳረፈበት ገላ ሰምበር በሰንበር ሆነዋል። ይህም ሌሊት ሌሊት በሚፈጸም ከዛፉ ወተት ለማምረት በተደረገ ጥረት ሳቢያ የተፈጠረ ነው። ጎማን ለመሥራት የሚያስችለውና ከዛፉ የሚገኘውን ወተት ማምረትም የሰለጠኑ ባለሙያዎች ሌሊት ከ9 ሰዓት ጀምሮ የሚከውኑት ተግባር ነው። ይህን ሥራ ለማቀላጠፍም ከ500 በላይ የሚሆኑ ሰራተኞች ላይና ታች ይላሉ። ሠራተኞቹም ራሳቸውን ከማስተዳደር ባለፈ በወዝ በላባቸው ለሀገር አዎንታዊ ተጠቃሚነት የሚውለውን ምርት ያቀርባሉ። የጎማ ዛፍ በተፈጥሮ ብዙ ወተት የሚይዘው ሌሊት ነው። ቀን የሰበሰበውን ወተት ሌሊት ያለ ስስት ይለግሳል። በዚህን ሰዓት ዛፉን አድምተው ወተት ሊያልቡ የተዘጋጁ ሠራተኞች በሰለጠኑት ሙያ መሠረት የፀሐይ መውጫና መግቢያ አቅጣጫን ቀድመው ይለያሉ። የፀሐዩን አቅጣጫ ከለዩ በኋላ በዛፉ ሰሜንና ደቡብ አቅጣጫ ጎን ላይ በስለታማ ቁስ በአንድ መስመር ቀጥ አድርገው በመፈቅፈቅ ለዛፉ ወተት መውረጃ ቦይ ያበጃሉ። በመቀጠል ሁለቱን መስመሮች ከፊት ለፊት የሚያገናኝ ሌላ መስመር በማበጀት የዛፉ ወተት መሰል ፈሳሽ ከስር ወደተቀመጠው ፈሳሽ መቀበያ ባልዲ ያለ ስስት ይፈሳል።   የጎማ ዛፍ ወተት ጠብታ ከእያንዳንዱ ዛፍ ስር ተሰብስቦ በብዙ ሊትር ተመዝኖ በበርሜል ይከማቻል። በአግባቡ የማጣራትና አሲድ ጨምሮ የማርጋት ሥራ ወደ ሚሰራበት ክፍል ይገባል። ወተቱ ከረጋ በኋላም ይታጠባል። ተድጦ የሚፈለገውን ያህል ቅርጽ ከያዘ በኋላ ጋቢ መስሎ ፀሐይ ላይ ይሰጣል።   በፀሐይ ኃይል ጠፈፍ እንዲል የተሰጣው ምርት የተያዘለት ሰዓት ሲጠናቀቅ በባህላዊ መንገድ ወደ ተዘጋጀው ጭስ ቤት ይላካል። በዚህ ክፍል ውስጥ ለዚሁ ተግባር የሚያገለግሉ በተለያየ ደረጃ የተዘጋጁ እሳት ማንደጃ ጉድጓዶች ይገኛሉ። ከፀሐይ ላይ ተሰጥቶ ወደ ውስጥ እንዲገባ የተደረገው ምርት በዚህ ክፍል ከ5 እስከ 6 ቀናት የተለያዩ የድርቀት ደረጃዎችን እየተሸጋገረ ይቆያል። በጥሩ ሁኔታ ቀይ ሆኖ ከደረቀ በኋላ ለጎማ ኢንዱስትሪ ጥሬ ዕቃ ሆኖ ለሽያጭ ዝግጁ ይሆናል።   ሁለት አስርተ ዓመታትን ያስቆጠረው የጎማ ልማትና ምርት ሥራ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባውን የጎማ ጥሬ ዕቃ በከፊል በመሸፈን በሀገራዊ ኢኮኖሚው ላይ የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። በኬሚካል ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን የጎማ ዛፍ ልማትና ምርት ፕሮጀክቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ ዘማች ሳድንስ እንደሚሉት፤ የጎማ ዛፍ አንድ ጊዜ ከተተከለ በኋላ ዓመቱን ሙሉ ምርት የሚሰጥ ዛፍ ነው። የወተት ምርት ለመስጠት ችግኙ ከተተከለ በኋላ ለሦስት ዓመታት ይቆያል።   በጉራፈርዳ ወረዳ ለምቶ ምርት እየሰጠ ካለው ዛፍ በወር ከ37 እስከ 40 ቶን የጎማ ዛፍ ጥሬ ምርት በመመረት ላይ ሲሆን ዘንድሮ ከ560 ቶን በላይ ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ በማቅረብ የዘርፉን የጥሬ ምርት ፍላጎት በከፊል ለመመለስ እየተሰራ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ከ87 ሺህ ሄክታር በላይ ለጎማ ዛፍ ምቹ መሬት እንዳላት ጥናቶች ያመለክታሉ። ይሁን እንጂ በስፋት ወደዚህ ዘርፍ በመግባት የዘርፉን ኢኮኖሚ መጠቀም አልተቻለም። የኬሚካል ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን የጎማ ዛፍ ልማትን ለማስፋፋት አቅዶ በጥናት ከተለዩ ቦታዎች መካከል በኦሮሚያ ክልል ኢሉአባቡር ዞን ከ2 ሺህ 500 ሔክታር በላይ መሬት ተረክቦ ችግኝ የማዘጋጀት ተግባር እያከናወነ ይገኛል። በዚህም የሀገር ውስጥ የጥሬ ምርት ፍላጎትን በሀገር ውስጥ በመሸፈን እና የተረፈውን ኤክስፖርት በማድረግ ከዘርፉ የውጭ ምንዛሬ ማግኘት የሚቻልበትን ዕድል ለመፍጠር ትኩረት መደረጉን አቶ ዘማች ጠቁመዋል። ባለሃብቶች ወደዚህ ዘርፍ ቢሰማሩ ሀገርን የሚጠቅሙ ውጤቶችን ማምጣት እንደሚቻልም አክለዋል። ኢትዮጵያ በየዘርፉ ያላት የኢኮኖሚ አቅም የዕድገት ጉዞዋ አቅሞች ናቸው። በተለይ ለም አፈሯ ከፍተኛ ፋይዳ ያላቸው ምርቶችን በማብቀል ለሀገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን ለዓለም ሀብት መፍጠር የሚያስችሉ መሆናቸውን በብዙ መንገድ ማረጋገጥ እየተቻለ ነው። ብዙም ትኩረት ያልተሰጠው የጎማ ዛፍ ልማትም ከእነዚህ አቅሞች አንዱ ነው። ያሉንን ጸጋዎች ለይቶ ለማልማትና ምርታማነትን ለመጨመር መንግሥት የሰጠውን ትኩረት መሠረት በማድረግ የጎማ ዛፍ ምቹ አጋጣሚዎችን ለይቶ መሥራት ከተቻለ ከዘርፉ በብዙ መጠቀም ይቻላል፡፡
ሶስት አስርት ዓመታትን የተሻገረው የኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ወዳጅነት
Feb 26, 2026 1062
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በአዘርባጃን ሪፐብሊክ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ዛሬ ማድረግ ጀምረዋል። ይህ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የአዘርባጃን ሪፐብሊክ ጉብኝት የሁለቱን ሀገራት የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጠናከር ማሳያ ነው። ይህ ጉብኝት የሁለትዮሽ ግንኙነቶችን የላቀ እና ትርጉም ያለው ደረጃ ያደርሰዋል።   ኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የጀመሩት አዘርባጃን እ.አ.አ በ1991 ነጻነቷን ማግኘቷን ተከትሎ ነው። የሀገራቱ ግንኙነት ከእ.አ.አ 1990ዎች መግቢያ አንስቶ እያደገ መጥቷል። አዘርባጃን እ.አ.አ በ2015 በኢትዮጵያ ኤምባሲ የከፈተች ሲሆን ይህም የሁለቱን ሀገራት የዲፕሎማሲ ትብብር እንዲጠናከር በር ከፍቷል። በቱርክዬ የሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ኢትዮጵያ ከአዘርባጃን ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ስራ የሚሸፍን ሲሆን ፖለቲካ፣ ትምህርት እና ባህል ሀገራቱ ካላቸው የትብብር መስኮች መካከል ተጠቃሽ ናቸው።   የሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እየጎለበተ መምጣቱን ከሚያመላክቱ ጉዳዮች መካከል በባለብዙ ወገን መድረክ በገለልተኛ ሀገራት ንቅናቄ (ናም) መድረክ በትብብር እየሰሩ መገኘታቸው ተጠቃሽ ነው። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2019 በአዘርባጃን ባኩ በተካሄደው 18ኛው የገለልተኛ ሃገራት ንቅናቄ (ናም) ጉባኤ ላይ ተሳትፋለች። የገለልተኛ ሀገራት ንቅናቄ 120 አባል ሃገራትን ያቀፈና ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቀጥሎ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የዓለም ሀገራትን በአባልነት የያዘ ስብስብ ነው። የኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ወዳጅነት የደቡብ ደቡብ ትብብር ማሳያ ተደርጎም ይወሰዳል። በሀገራቱ መካከል ተከታታይ የሆኑ የባህል ልውውጥ መድረኮች ተካሄደዋል። ለዚህም እ.አ.አ በ1960ዎቹ የኢትዮጵያ ተማሪዎች በአዘርባጃን የትምህርት እድል አግኝተው ይከታተሉ እንደነበር መረጃዎች ያሳያሉ። ከኢኮኖሚ አንጻር እ.አ.አ በ2017 በአዘርባጃን የተካሄደው የሁለቱ ሀገራት የቢዝነስ ፎረም ተጠቃሽ ነው። በወቅቱ ጨርቃጨርቅን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች የተሰማሩ የኢትዮጵያ የንግድ ማህበረሰብ አባላት ተሳትፈዋል። በወቅቱ ሀገራቱ እርስ በእርስ ያላቸውን የንግድ ልውውጥ ምጣኔ ለማሳደግ የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ባለስልጣናት መካከል የሚደረጉ የጉብኝት ልውውጦች እያደጉ መጥተዋል።   ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በግንቦት ወር 2016 ዓ.ም በአዘርባጃን ጉብኝት ማድረጋቸወ ይታወሳል። ኢትዮጵያና አዘርባጃን በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በቴክኖሎጂና በሌሎች ዘርፎች ያላቸውን ትብብር የበለጠ ማሳደግና በጋራ መስራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ዙሪያ መምከራቸውም እንዲሁ። ምክክሩ እጅግ ውጤታማ የነበረ ሲሆን የሁለቱን ሀገራት ህዝብ ዕድገት እና ብልፅግና በመደጋገፍና በትብብር መንፈስ ለመስራት ስምምነት ላይ መድረሳቸውም በወቅቱ ተገልጿል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ከአዘርባጃን የሀገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስትር ኮሎኔል-ጀነራል ኢይቫዞቭ ቪላያት ሱለይማን ጋር በነበራቸው ውይይት የደህንነት ጉዳዮችን ጨምሮ የኢትዮጵያን እና አዘርባጃን የሁለትዮሽና የባለብዙ ወገን ትብብሮችን ማጠናከር የሚያስችሉ ቀጣይ ስራዎች ላይ መክረዋል። በውይይቱም በመረጃ፣ በፀጥታና ደህንነት ዘርፎች የጋራ ትብብር አቅም ግንባታና ሌሎች ጉዳዮች ሁለቱን ሀገራት ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን በጋራ ለመፈጸም መስማማታቸውን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ መግለጻቸው ይታወሳል።   እ.አ.አ በ2017 በወቅቱ የአዘርባጃን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩት ኤልማር ማማድያሮቭ በኢትዮጵያ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸውና የኢትዮጵያ እና አዘርባጃን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች በቋሚነት የፖለቲካ ምክክር ማድረግ የሚያስችላቸውን የጋራ መግባቢያ ስምምነት መፈራረማቸው ይታወቃል። የአዘርባጃን የፐብሊክ ሰርቪስ እና ማኅበራዊ ፈጠራ ተቋም ሊቀ መንበር ኦልቪ ሜዲዬቭ የብሔራዊ ቤተመንግሥት እና የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎትን በሰኔ ወር 2017 ዓ.ም ጎብኝተዋል። ኦልቪ ሜዲዬቭ በወቅቱ ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ጋር ተወያይተዋል።   የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ(ዶ/ር) በጥር ወር 2017 ዓ.ም በአዘርባጃን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ያልቺን ራፊየቭ የተመራ ልዑክ ጋር በአዲስ አበባ ተወያይተዋል፡፡ በውይይታቸውም ኢትዮጵያ ወደ አዘርባጃን የምትልካቸው ምርቶች ብዝኀነትን ለማሳደግና ለማስፋፋት ቁርጠኛ መሆኗን ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ(ዶ/ር) ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያ ወደ አዘርባጃን ከምትልካቸው ምርቶች መካከል ሰሊጥ፣ የተቆላ ቡና፣ ተልባ፣ የፍየል እና የበግ ሥጋን ጨምሮ ሌሎች ምርቶች እንደሚገኙበት ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡   በአዘርባጃን የመከላከያ ኢንዱስትሪ ሚኒስትር ቩጋር ሙስታፋይ የተመራ ልዑክ በህዳር ወር 2018 ዓ.ም በኢትዮጵያ ከመከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሀመድና ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አካሂዷል፡፡ በውይይቱ ኢትዮጵያ እና አዘርባጃን በመከላከያ ዘርፍ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር መስማማታቸው ይታወሳል። በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካና ንግድ ትብብር ላይ ያተኮረው ሶስተኛ የኢትዮ-አዘርባጃን የውይይት መድረክ በጥር ወር 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ተካሂዷል። ከውይይቱ በኋላ ሀገራቱ የኢኮኖሚ እና የንግድ ግንኙነታቸውን ለማሳደግና ተጨማሪ እድሎችን መፈተሽ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይም መግባባት ላይ ደርሰዋል። 29ኛው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 29) በህዳር ወር 2017 ዓ.ም በአዘርባጃን መካሄዱ ይታወቃል። በጉባኤው ኢትዮጵያ በፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በተመራ ልዑክ ተሳትፎ አድርጋለች። በወቅቱ የኢትዮጵያ ልዑክ ከአዘርባጃን ባለስልጣናት ጋር በመወያየት ሀገራቱ በአካባቢ ጥበቃ፣ አየር ንብረት ለውጥ መከላከል እና አረንጓዴ ልማት ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር በቁርጠኝነት ለመስራት የጋራ መግባባት ላይ ደርሰዋል። በሀገራቱ መካከል ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የተደረጉ ውይይቶችና የልምድ ልውውጦች የሁለትዮሽ ዲፕሎማሲያዊ ትብብር እየጠነከረ መምጣቱን ያሳያል። ኢትዮጵያ እና አዘርባጃን በንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ግብርና፣ ዲጂታላይዜሽን፣ ትምህርት እና ባህልን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች ትብብራቸውን ለማጠናከር ይሻሉ።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በአዘርባጃን ሪፐብሊክ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ዛሬ ማድረግ መጀመራቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። የኢትዮጵያ እና የአዘርባጃን ግንኙነት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየጠነከረ መምጣቱን የገለጸው ጽህፈት ቤቱ ለዚህም ጉልህ ማሳያው በጠንካራ ትብብር የቀጠለው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ጎልቶ እንደሚታይ አንስቷል። የዛሬው የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የአዘርባጃን ሪፐብሊክ ጉብኝትም የዚሁ የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጠናከር ማሳያ መሆኑን ጠቁሟል። ይህ ጉብኝት የሁለትዮሽ ግንኙነቶችን የላቀ እና ትርጉም ያለው ደረጃ እንደሚያደርስ ይጠበቃል ሲልም ጽህፈት ቤቱ አመልክቷል። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጉብኝት በመሪ ደረጃ የሚደረግ መሆኑ በሁለቱ ሀገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ውስጥ ትልቅ ትርጉም ይሰጠዋል። ሶስት አስርት ዓመታትን የተሻገረው የኢትዮጵያ እና አዘርባጃን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በሁለትዮሽ፣ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚሸጋገር የቅርብ ዓመታት ውይይቶች እና ጉብኝቶች ማሳያ ናቸው።
የኢትዮጵያ የስኬት ጉዞ …
Feb 26, 2026 672
(በሙሴ መለሰ) ኢትዮጵያ በየዘርፉ እያስመዘገበቻቸው የሚገኙት ስኬቶች በተለያዩ የዓለም መድረኮች በምሳሌነት እያስጠቀሳት ይገኛሉ። ኢትዮጵያ በአምስቱ ዋና ዋና የኢኮኖሚ አምዶቿ ማለትም በግብርና፣ በኢንዳስትሪ፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም እና በቴክኖሎጂ ዘርፎች እየተመዘገቡ የሚገኙ ስኬቶችን ቀጥለን እንዳሥሣለን። የስንዴ ምርታማነት ስኬት ኢትዮጵያ በግብርና በተለይ በሌማት ትሩፋት እና በስንዴ ልማት ምርታማነትን በከፍተኛ ደረጃ ስኬት ያስመዘገበችባቸው መስኮች ናቸው። ቀደም ሲል ስንዴን ከውጭ ለማስገባት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ታወጣ እንደነበር መረጃዎች ይጠቁማሉ። ከለውጡ መንግስት ወዲህ ግን በተለይ ለስንዴ ልማት በተሰጠው ከፍተኛ ትኩረት የግብርና ሜካናይዜሽን በመጠቀም ምርት እና ምርታማነትን በከፍተኛ መጠን ማሳደግ በመቻሉ ከራስ ፍላጎት ባለፈ ለውጭ ገበያ በማቅረብ ላይ ትገኛለች። ይህ ውጤታማነቷም በተለያዩ የዓለም ዓቀፍ ተቋማት ጭምር እውቅና አስችሯታል። ለስንዴ ምርት እና ምርታማነት ማደግ ዘመናዊ የመስኖ ሥርዓቶች፣ የኩታ ገጠም አስተራረስ ዜዴ፣ የግብርና ሜካናይዜሽን ስልቶችና የግብርና ኢኒሼቲቮች በዋና ምክንያትነት ይጠቀሳሉ። በዚህ መነሻነት ነው የአፍሪካ ኅብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽን ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ የኢትዮጵያ የስንዴ ምርታማነት ለአፍሪካ አርዓያነት ያለው መሆኑንና በስንዴ ልማት ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ያስመዘገበችው ለውጥ ከፍተኛ መነሳሳት መፍጠሩን ጠቅሰዋል። ይህን የኢትዮጵያን ውጤታማነት መነሻ በማድረግም የአፍሪካ ሀገራት እንዲተገብሩት መክረዋል። በተመሳሳይ በ2016 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተባበሩት መንግሥታት የምግብ እና የእርሻ ድርጅት የከበረውን የፋኦ አግሪኮላ ሜዳሊያ መሸለማቸው ይታወቃል። ሽልማቱ በምግብ ዋስትናና በተመጣጠነ የምግብ አቅርቦት ላሳዩት ትጋት፣ ፈጣን፣ ተለዋዋጭና ፈታኝ በሆነው ከባቢያዊ ሁኔታ በስንዴ ምርት ራስን ለመቻል በተከተሉት ፈጠራዊ መፍትሔ ዕውቅና ለመስጠት የተበረከተ ነው። የኢትዮጵያ የስንዴ ምርታማነት ስኬት የግብርናው አብዮት ማሳያ ሲሆን፤ ራስን መቻል እና ለአፍሪካ መብቃትን ያለመ ነው። ዲፕሎማሲያዊ ስኬት   በሰላም ግንባታ፣ ግጭት አፈታት እና አኅጉራዊ ትሥሥር ረገድ ሚናዋን እየተወጣች ያለችው ኢትዮጵያ፤ በዲፕሎማሲው መድረክም ተደማጭነቷ እያደገ መጥቷል። በሰላም ማስከበር፣ አረንጓዴ ዐሻራና በሌሎች ዐበይት ጉዳዮች ኢትዮጵያ በቅርብ ጊዜያት በዓለም መድረኮች ስሟ ከፍ ብሎ እየተሰማ ነው።   የቱርክዬ ፕሬዚዳንት ረጀብ ጠይፕ ኤርዶዋን፣ የሕንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ የኬንያ ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ፣ የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ይ፣ የአሜሪካ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ክርስቶፈር ላንዳው፣ የእስራኤል ፕሬዚዳንት አይዛክ ሄርዞግ እና የሌሎች ሀገራት ባልሥልጣናት የቅርብ ጊዜ የኢትዮጵያ ጉብኝቶች የሀገሪቱን የጂኦ ፖለቲካዊ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ብሎም የዲፕሎማሲ ተደማጭነት እያደገ መምጣት ያሳያሉ። ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲው መስክ ብሔራዊ ጥቅሟን ከማስጠበቅ ባለፈ በዓለም መድረክ የአፍሪካ ድምጽ እየሆነች ትገኛለች።   አረንጓዴ ዐሻራ - ሌላኛው የኢትዮጵያ ስኬት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት በሀገር አቀፍ ደረጃ ሐምሌ 2011 ዓ.ም በተጀመረው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር፤ እስከአሁን ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞች ተተክለዋል። በ2011 ዓ.ም 17 ነጥብ 2 በመቶ የነበረው የኢትዮጵያ የደን ሽፋን፤ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት በአረንጓዴ ዐሻራ በተከናወነው ሥራ አሁን ላይ ከ23 በመቶ በላይ ደርሷል። በኢትዮጵያ በተካሄደው 2ኛው የዓለም የምግብ ሥርዓት ጉባዔ የአረንጓዴ ዐሻራ ሥራው ዕውቅና ተችሮታል። በተጨማሪም በ2ኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባዔ የአረንጓዴ ዐሻራ ሥራዋን ኢትዮጵያ ባስተዋወቀችበት ወቅት፤ የአፍሪካ ሀገራት ትልቅ ተምሳሌት የሚሆን ኢኒሼቲቭ መሆኑንም በምሳሌነት ጠቅሰውታል። ኢትዮጵያ ለጎረቤቶቿ ችግኝ በመስጠት የአካባቢ ጥበቃ የጋራ አጀንዳ መሆኑን አሳይታለች። ይህም "አረንጓዴ ዲፕሎማሲ" በመባል የሚታወቅ ሲሆን፤ በሀገራት መካከል በጎ ግንኙነትን ለማዳበር አስተዋጽኦ አበርክቷል።   የግዙፍ (ሜጋ) ፕሮጀክቶች ግንባታና ምረቃ በወርሃ ጳጉሜን 2017 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተመረቀው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለአፍሪካ የኢነርጂ ትሥሥር ውጥን ትልቅ የምሥራች ነው። የጎረቤት ሀገራት ከኢትዮጵያ የሚያገኙት የኤሌክትሪክ ሀይል አቅርቦትም ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከር ያስችላል። በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙ የሀገራት መሪዎች ባደረጉት ንግግር የሕዳሴ ግድብ የአፍሪካ ራስን የመቻል ምልክት እና የኢትዮጵያ አይበገሬነት ተምሳሌት መሆኑን በአጽንኦት አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፤ የኒውክሌር ማበልጸጊያ እንደሚገነባ፣ የጋዝ ፋብሪካ እንደሚመረቅ፣ የነዳጅ ማጣሪያ ዕውን እንደሚሆን፣ በአፍሪካ ግዙፍ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እንደሚገነባ፣ የማዳበሪያ ፋብሪካን ጨምሮ የ1 ነጥብ 5 ሚሊየን ቤቶች ግንባታ እንደሚከናወን ጉባ ላይ ማብሠራቸው ይታወሳል።   ይህን ተከትሎም በሶማሌ ክልል የጋዝ ፋብሪካ ተመርቋል፣ የቢሾፍቱ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታም ተጀምሯል። የሌሎች መሠረተ ልማቶች ግንባታ እና የዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛል። እየተገነባ ያለው ኮይሻ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫም ለኢነርጂ አቅርቦት ዕድገት የበኩሉን ሚና እንደሚጫወት መገለጹ ይታወሳል።   የኮሪደር ልማት እና የከተማ ማዘመን ሥራዎች የኮሪደር ልማት ኢኒሼቲቮች የትራንስፖርትን ጨምሮ የተለያዩ መሠረተ ልማቶች እንዲዘምኑ፣ የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች እንዲስፋፉ፣ የንግድ ተቋማት አሰራር እንዲዘምን፣ አምፊ ቴአትርን ጨምሮ የኪነ-ጥበብ መሠረተ ልማቶች እንዲገነቡ፣ የስፖርት መሠረተ ልማቶች ግንባታ እንዲከናወን የራሳቸውን አስተዋጽኦ አበርክተዋል። የኮሪደር ልማቱ አዲስ አበባን ጨምሮ በርካታ የክልል ከተሞችን ከማስዋብ ባለፈ ዜጎች በንጹህ አካባቢ እንዲኖሩ አስችሏል። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት(አይ ኤም ኤፍ) ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክሪስታሊና ጆርጂዬቫ እ.አ.አ በ2025 ስለ አዲስ አበባ ሲናገሩ፤ ከተማዋን ጊዜ ወስደው መመልከታቸውንና ከፍተኛ መሻሻል እንዳዩ መግለጻቸው አንዱ ማሳያ ነው። የኬንያ የፓርላማ አባል ጁኔት መሐመድም አዲስ አበባን የአፍሪካ አዲሷ ዱባይ ሲሉ አድንቀው፤ አዲስ አበባ እያስመዘገበች ያለው ፈጣን ዕድገት ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ምሳሌ መሆኑንም ገልጸዋል። በተጨማሪም የተለያዩ ዲፕሎማቶች፣ የውጭ ሀገር ዜጎች እንዲሁም የልማት አጋሮች ለአዲስ አበባ የከተማ መዘመንና ለውጥ ምስክርነታቸውን መስጠታቸው አይዘነጋም።   በሰው ሠራሽ አስተውሎት ረገድ ኢትዮጵያ ለቴክኖሎጂና ሰው ሠራሽ አስተውሎት ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ከአምስት ዓመታት በፊት የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትን አቋቁማ ወደ ሥራ ገብታለች። በዘርፉ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በሁለተኛና ሦስተኛ ዲግሪ ትምህርት እየተሰጠም ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓልን አስመልክቶ ባካሄደው መድረክ ላይ፤ ፈጥነን ልጆቻችንን ካዘጋጀን ሰው ሠራሽ አስተውሎትን እንደ ተለያዩ ምርቶች በቀላሉ መጠቀም እንችላለን ሲሉ አጽንኦት ሰጥተዋል። ለሰው ሠራሽ አስተውሎት ፖሊሲ እና ስትራቴጂ ተዘጋጅቶ እየተተገበረ መሆኑን ገልጸው፤ ኢትዮጵያ የምትገነባው የኤ አይ ዩኒቨርሲቲም የኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ብዙ ችግሮችን ይፈታል ብለዋል። ኢትዮጵያ ለሰው ሠራሽ አስተውሎት መሠረት እየጣለች መሆኗንም አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ ዘመኑን የዋጀ ዕይታ ለዲጂታል ዘመን ለውጦች ምላሽ ከመስጠት ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትንም ይፈጥራል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ እና የኢትዮጵያ ሰው ሠራሽ አስተውሎት ኢንስቲትዩት ኢትዮጵያን በዲጂታል ዘርፉ ወደ ቀጣይ ምዕራፍ የማሸጋገር ዐቅም አላቸው።   ኢትዮጵያ - የአፍሪካ የአቪዬሽን ማዕከል የአፍሪካ አቪዬሽን ምልክት የሆነው ግዙፉ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፤ ኢትዮጵያን ከቀሪው ዓለም እና አፍሪካን ርስ በርስ በማገናኘት በኩል የመሪነት ሚናውን እየተወጣ ነው። የአየር መንገዱ የመንገደኞች እና የካርጎ አገልግሎቶች የንግድ፣ የቱሪዝም እና ዓለምአቀፍ የቢዝነስ ግንኙነቶች እንዲጠናከሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተም ይገኛል። በተያዝው በጀት ዓመት የመጀመሪያ አጋማሽም አየር መንገዱ 10 ነጥብ 64 ሚሊየን ሰዎችን ማጓጓዝ መቻሉ ለመሪነቱ ትልቅ ማሳያ ሆኖ ይወሰዳል። በሌላ በኩል በአፍሪካ ግዙፍ የሆነው ቢሾፍቱ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ተጀምሯል። የዚህ ግንባታ መጀመር ኢትዮጵያ በአፍሪካ አቪዬሽን ያላትን የመሪነት ሚና አጠናክሮ ለማስቀጠል ሁነኛ ሚና አለው።   ሌላኛው የኢትዮጵያ ስኬት - ቱሪዝም ኢትዮጵያ በታሪክ፣ ባህል፣ በተፈጥሯዊ እና ሰው ሠራሽ የቱሪዝም መዳረሻዎች የታደለች ናት። እነዚህም ጎብኚዎችንና ተመራማሪዎችን መሳባቸውን ቀጥለዋል። መንግሥት እንደ አንድ የኢኮኖሚ ምሰሶ ወስዶ እየሠራበት በሚገኘው የቱሪዝም ዘርፍ በተከናወኑ ሥራዎች አበረታች ውጤቶች ተገኝተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት፤ በገበታ ለሸገር፣ በገበታ ለሀገር እና በገበታ ለትውልድ አማካኝነት የተከናወኑ ሥራዎች የቱሪዝም ፀጋን ከመግለጥ ባለፈ የገቢ መጠንን እያሳደጉም ይገኛሉ። በቅርቡ በሶማሌ ክልል የተመረቀው እና የገበታ ለትውልድ ሥራ አካል የሆነው የሸበሌ ሪዞርት የዚሁ ሥራ ማሳያ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በምረቃው ወቅት፤ ሪዞርቱ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ የገባነውን ቃል በተግባር ያረጋገጠ የምሥራቁ የሀገራችን ክፍል ትልቅ ሥራ ነው ማለታቸው ይታወሳል። በአዲስ አበባ የሚገኙት የወዳጅነት ዐደባባይ፣ አንድነት ፓርክ፣ ሳይንስ ሙዚየም እና ሌሎችም ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻዎች ሆነዋል። የኮሪደር ልማቱም የመዲናዋን መልክ በአዲስ ሁኔታ በመግለጥ ጎብኚዎችን እየሳበ ነው። በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በግብርና፣ በዲፕሎማሲ፣ በኢኖቬሽን፣ በመሠረተ ልማት፣ በከተማ ማዘመንና ኮሪደር ልማት፣ ቱሪዝምን ጨምሮ በሌሎች መስኮች ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች የራሷን መጻኢ ጊዜ ብሩኅነት ያመላክታሉ። የኢትዮጵያ ስኬቶች ብሎም ስትራቴጂካዊ ራዕይ ጊዜውን የሚመጥን ዕድገትን በትጋትና በጋራ ትብብር የመሥራት ውጤትን የሚያሳዩ ናቸው። ኢትዮጵያ ለዛሬ ብቻ እየሠራች አይደለም፤ ቀጣይ ለሚመጡ ትውልዶች መሠረት እየጣለችም እንጂ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም