መጣጥፍ - ኢዜአ አማርኛ
መጣጥፍ
ዕድሜ ያልገደበው የልማት አርበኝነት
Jan 14, 2026 228
ዕድሜ ያልገደበው የልማት አርበኝነት ብርቱዎች ነገን በማሰብ ሁሌም ታትረው ይሰራሉ፤ ይደክማሉ፤ ይጥራሉ…ለቀጣዩ ትውልድም ጥሪት በማስቀመጥ አሻራቸውን ያኖራሉ። አገር የምትገነባው በትውልድ ቅብብሎሽ ነው። “አባት ያበጀው፤ ለልጅ ይበጀው” እንደሚባለው ልጆች ከአባቶቻቸው ያገኙትን ጥሪት በአዲስ እውቀትና አሰራር ለአገር እድገት በሚበጅ መልኩ አጠናክረው መጠቀማቸው አይቀርም። “ዕድሜ ጸጋ ነው” የሚለው አባባል አንዳንዴ በዕድሜ ብንገፋም ጠንክረን ከሰራን ብዙ ነገር እናያለን ከሚለው ጋር የተያያዘ ነው። በሰቆጣ ከተማም እድሜ ሳይገድባቸው በልማት ውጤታማ የሆኑ ግለሰቦች ለዚህ ማሳያ ናቸው። የከተማዋ ነዋሪ የ67 ዓመቱ አቶ ብርሃኑ አወቀ እና የ83 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ አቶ ታደሰ አዳነ ዕድሜያቸው ቢገፋም ጠንክሮ ከተሰራ ውጤታማ መሆን እንደሚቻልና ዕድሜ ጸጋ ሆኖ ብዙ ለውጥ ማየት እንደሚቻል ማሳያ ናቸው። ግለሰቦቹ ከዕድሜ ብዛት ጉልበቴ ደከመ፣ አይኔ ፈዘዘ፣ እጄም ተሳሰረ…ሳይሉ ጊዜያቸውን በደን፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሥራ በማሳለፍ ለወጣቶች የልማት አርአያነት ያለው ተግባር እየፈጸሙ ነው። አቶ ብርሃኑ አወቀ በሰቆጣ ከተማ ዳርቻ የሚገኝ አለቱ ያገጠጠና የተራቆተ አካባቢን ከሌላ አካባቢ ለም አፈር በማምጣትና በመደልደል አትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም ደን በማልማት ውጤታማ ስራ እያከናወኑ ነው። ከመንግስት ሥራ በጡረታ ከወጣሁ ጀምሮ ጠንክሬ በመስራት የምለወጥበትን ሥራ ማሰብ ስነበረብኝ፤ የቆሻሻ መጣያ ሆኖ ለዘመናት የቆየን ጭንጫ መሬት ጠርጌና ደልድዬ ማልማት ችያለሁ ይላሉ ወደኋላ መልስ ብለው የተነሱበትን ሁኔታ ሲያስታውሱ። ግማሽ ሄክታር በማይሞላ መሬት ላይ ፓፓያ፣ ሙዝ፣ ዘይቱና፣ ጌሾ፣ ቡና፣ ማንጎና አቮካዶ አልምተዋል። በተጨማሪም ቆስጣ፣ ቲማቲም፣ ጥቅል ጎመንና ሽንኩርት በማምረት ከቤት ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ጥሪት አፍርተዋል። ጊዜን በአግባቡ ተጠቅሞ ተግቶ መስራት ከተቻለ ሀብት ማፍራትና ህይወትንም መለወጥ እንደሚቻል የገለጹት አቶ ብርሀኑ፣ ወጣቱም ከእሳቸው የሥራ ትጋት በመማር በአካባቢው ያለውን ፀጋ ለይቶ በማልማት ሊጠቀም ይገባል ሲሉ ይመክራሉ። ሌላው የ83 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ አቶ ታደሰ አዳነ ባለፉት 18 ዓመታት በተሰማሩበት የአትክልትና ደን ልማት ሥራ የአካባቢያቸውን ገጽታ ቀይረዋል። የዕድሜ ዘመናቸውን በውትድርናና በመንግስት ሠራተኝነት በማገልገል ሃገራዊ ግዳጃቸውን ሲወጡ ነው የቆዩት። ከመንግስት ሥራ በጡረታ ከተገለሉ በኋላም ቤት ውስጥ መቀመጥን አልመረጡት። አካፋና ዶማቸውን ይዘው ባላቸው ትንሽ መሬት ላይ ጌሾ፣ ዘይቱና እና ማንጎ በማልማት ምርቱን ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ሆነዋል። በአካባቢያችን ያሉ ፀጋዎችን በአግባቡ ለይተን ማልማት ከቻልን ድህነትን ማስወገድ የሚከብድ አይሆንም ያሉት አቶ ታደሰ፣ የተራቆተና በጎርፍ የተጎዳን መሬት በማልማት አካባቢውን ሳቢና ማራኪ ማድረጋቸውን ነው የገለጹት። ወጣቱም ከእሳቸው አርአያነት ያለው ተግባር በመማር በአካባቢው እጁ ላይ ባለ ሀብት ሰርቶ መለወጥ እንደሚቻል በተግባር ማሳየት እንዳለበት መክረዋል። የዋግኸምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ግብርና መምሪያ የአትክልትና ፍራፍሬ መስኖ ውሃ አጠቃቀም ቡድን መሪ አቶ ደሳለኝ አዳነ እንደገለጹት፤ በብሔረሰብ አስተዳደሩ 24ሺህ 847 አርሶ አደሮች በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተዋል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል ዕድሜ ሳይገድባቸው ወደ ልማት የገቡ አረጋዊያን እያከናወኑት ያለው የግብርና ልማት ሥራ ለወጣቱ ትልቅ ትምህርት እንደሚሆንም ተናግረዋል። ከእነሱ ልምድ በመውሰድ በዞኑ ወጣቶች፣ ሴቶችና አረጋዊያን በጓሮና ባላቸው መሬት ላይ አትክልትና ፍራፍሬ እንዲያለሙ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸው ይህም በዞኑ የሚስተዋለውን የስርዓተ ምግብ ችግር ለማሻሻል ያግዛል ብለዋል።
ከማላጋ እስከ አፍሪካ ዋንጫ፤ የሞሮኮው አዲስ እንቁ ብራሂም ዲያዝ
Jan 13, 2026 253
የግል ክህሎት፣ ፈጣን አስተሳሰቡ እና በጠባብ ክፍተቶች ውስጥ ሰብሮ የመግባት አቅሙ ሙገሳ እንዲጎርፍለት አድርጓል። አንድ ለአንድ ሲገናኝ ተከላካዮችን በፈጣን አካላዊ ቅልጥፍና እና በድንገት አቅጣጫ በመቀየር የሚያልፍበት መንገድ እንዲሁም የመፍጠር አቅሙ የተመልካቾችን ቀልብ የሚይዝ ነው። የአማካይ እና የአጥቂ መስመርን በማገናኘት እና በአስገራሚ ሁኔታ አጭር ኳሶችን በማቀበልም የተዋጣለት ተጫዋች ነው ማለት ይቻላል። በቦታ አያያዙ የእግር ኳስ ልኅቀቱ ከፍተኛ ነው የሚል አድናቆት ከእግር ኳስ ባለሙያዎች አግኝቷል። ኳስን ሲያንከባልልም ለዐይን ይስባል። ከክህሎቱ እና ከማራኪ እንቅስቃሴው ባለፈ ወደ ኋላ እየመለሰ ተከላካዮችን ያግዛል፣ ኳስ ይነጥቃል። ይህ ተጫዋች የ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ክስተት የሆነው የሞሮኮው ብራሂም ዲያዝ ነው። የ26 ዓመቱ የሪያል ማድሪድ የክንፍ መስመር ተጫዋች ዲያዝ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ አምስት ጨዋታዎችን አድርጎ አምስት ግቦችን በማስቆጠር የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን እየመራ ነው። አዘጋጇ ሞሮኮ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ መክፈቻ ኮሞሮስን 2 ለ 0 ስታሸንፍ የውድድሩን የመጀመሪያ ግብ አስቆጥሯል። ብራሂም አብዱልቃድር ዲያዝ የተወለደው እ.አ.አ ኦገስት 3 ቀን 1999 በስፔን ማላጋ ግዛት ነው። እናቱ ስፔናዊ አባቱ ሞሮኳዊ ናቸው። ዲያዝ ያደገው በማላጋ ነው። እግር ኳስንም በአንዳሉሺያዊቷ ከተማ ሲጫወት ቆይቷል። በ16 ዓመቱ ካደገበት ማላጋ በመውጣት እ.አ.አ በ2015 ወደ ማንችስተር ሲቲ ወጣት አካዳሚ በ200 ሺህ ፓውንድ ወጪ ተዘዋወረ። ዲያዝ እ.አ.አ ሴፕቴምበር 21 ቀን 2016 በካራባኦ ካፕ (በቀድሞ አጠራሩ ሊግ ካፕ) ማንችስተር ሲቲ ከስዋንሲ ሲቲ ባደረገው ጨዋታ በ80ኛው ደቂቃ በኬሌቺ ኢናቺዩ ተቀይሮ በመግባት ለውኃ ሰማያዊዎቹ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የመጀመሪያውን ጨዋታ ካደረገ ከሶስት ቀናት በኋላ ከማንችስተር ሲቲ ጋር ለሶስት ዓመታት የሚያቆየውን ፕሮፌሽናል ኮንትራት ተፈራርሟል። እ.አ.አ ኖቬምበር 21 ቀን 2017 ማንችስተር ሲቲ ከፌይኖርድ ሮተርዳም ጋር ባደረገው የሻምፒዮናስ ሊግ ጨዋታ ላይ የመጀመሪያ የአውሮፓ መድረክ ጨዋታውን ማድረግ ችሏል። በወቅቱ ብራሂም ስተርሊን መደበኛ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በጭማሪ ሰዓት ላይ ነበር ተቀይሮ የገባው። ዲያዝ በውኃ ሰማያዊዎቹ ማልያ ቋሚ አሰላለፍ ውስጥ ገብቶ የተጫወተው እ.አ.አ ዲሴምበር 19 ቀን 2017 ነው። ማንችስተር ሲቲ ከሌስተር ሲቲ በካራባኦ ካፕ ጨዋታ ላይ ለ88 ደቂቃዎች ተሰልፎ ተጫውቷል። እ.አ.አ ጃንዋሪ 20 ቀን 2018 ማንችስተር ሲቲ ኒውካስትል ዩናይትድን 3 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። በወቅቱ ማንችስተር ሲቲ የሊጉን ዋንጫ ያነሳ ሲሆን፤ በውድድር ዓመቱ አራት ጨዋታዎች ላይ ብቻ ተሳትፎ ያደረገው ብራሂም ዲይዝ የሜዳሊያ ሽልማት አግኝቷል። እ.አ.አ ኦገስት 5 ቀን 2018 ማንችስተር ሲቲ ቼልሲን 2 ለ 0 ባሸነፈበት የኮሙዩኒቲ ሺልድ ጨዋታ ላይ በፊል ፎደን ተቀይሮ በመግባት ለ15 ደቂቃዎች ተጫውቷል። ዲያዝ እ.አ.አ 2018/19 ማብቂያ ላይ ማንችስተር ሲቲ ፉልሃምን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የመጀመሪያ ግቦቹን ለሲቲ አስቆጥሯል። በማንችስተር ሲቲ ያለው ውል እ.አ.አ 2019 ሊጠናቀቅ በተቃረበበት ወቅት ስሙ ከዝውውር ጋር በስፋት ይነሳ ነበር። ዲያዝ እ.አ.አ ጥር 2019 በ17 ሚሊዮን ዩሮ ከማንችስተር ሲቲ ወደ ሪያል ማድሪድ ተዘዋወረ። ለስድስት ዓመታት የሚያቆየውን ውልም ፈርሟል። የክንፍ ተጫዋቹ የመጀመሪያ ጨዋታውን በነጮቹ ማልያ ያደረገው እ.አ.አ ጥር 9 ቀን 2019 ሪያል ማድሪድ ሌጋኔን በስፔን ጥሎ ማለፍ ዋንጫ 3 ለ 0 ባሸነፈበት ወቅት ነው። ከአራት ቀናት በኋላ በስፔን ላሊጋ ሪያል ማድሪድ ሪያል ቤቲስን 2 ለ 1 ባሸነፈበት ጨዋታ ተቀይሮ በመግባት በሊጉ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። የመጀመሪያ ግቡን ለማስቆጠር ሶስት ወራትን ጠብቋል። እ.አ.አ ግንቦት 12 ቀን 2019 ሪያል ማድሪድ በላሊጋው በሪያል ሶሲዬዳድ 3 ለ 1 ሲሸነፍ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። በወቅቱ ዲያዝ ስድስት ጨዋታዎች ላይ በላሊጋው የተጫወተ ሲሆን፤ በመጀመሪያ ዓመቱ የሊጉን ዋንጫ አንስቷል። ሪያል ማድሪድ እ.አ.አ በ2021/21 የውድድር ዓመት ብራሂም ዲያዝ ወደ ኤሲ ሚላን በውሰት ማምራቱን ይፋ አደረገ። ዲያዝ ሚላን እ.አ.አ መስከረም 27 ቀን 2020 ክሮቶኔን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ የመጀመሪያ ግቡን ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ ግንቦት 2021 ኤሲ ሚላን ጁቬንቱስን 3 ለ 0 ሲያሸንፍ ያስቆጠረው ግብም ተጠቃሽ ነው። ዲያዝ በኤሲ ሚላን የውሰት ውሉ ሲያበቃ በድጋሚ ለሁለት ዓመታት በውሰት የሚቆይበት ስምምነት ሪያል ማድሪድ ከጣልያኑ ክለብ ጋር የተፈራረመ ሲሆን፤ ውሉ ሚላን ተጫዋቹን የማቆየት መብት ሰጥቶታል። እ.አ.አ መስከረም 15 ቀን 2021 ኤሲ ሚላን በሻምፒዮንስ ሊጉ የ3 ለ 2 ሽንፈት ሲያስተናግድ የመጀመሪያ የአውሮፓ መድረክ ግቡን አስቆጥሯል። በ2023 ኤሲ ሚላን ቶተንሃም ሆትስፐርስን በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ጥሎ ማለፍ 1 ለ 0 ሲያሽንፍ ብቸኛውን ግብ ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ በ2023 ሰኔ ወር ላይ ሪያል ማድሪድ ዲያዝ ከኤሲ ሚላን የሶስት ዓመታት የውሰት ቆይታ በኋላ ወደ ክለቡ መመለሱን አሳውቋል። ተጫዋቹ በኤሲ ሚላን ቆይታው 91 ጨዋታዎችን አድርጎ 13 ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ዲያዝ ወደ ሪያል ማድሪድ ከተመለሰ በኋላ ኮንትራቱን እስከ 2027 አራዝሟል። እ.አ.አ መስከረም 27 ቀን 2023 ወደ ክለቡ ከተመለሰ በኋላ ሪያል ማድሪድ ላስ ፓልማስን 2 ለ 0 ባሸነፈበት ጨዋታ ግብ አስቆጥሯል። የክንፍ መስመር ተጫዋቹ ሪያል ማድሪድ በሀገር ውስጥ እና በአውሮፓ መድረክ በሚያደርጋቸው ጨዋታዎች ላይ ግብ በማስቆጠር እና ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን አመቻችቶ በማቀበል ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል። ዲያዝ እስከ አሁን ለሪያል ማድሪድ ባደረጋቸው 129 ጨዋታዎች 20 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ከነዚህም ውስጥ 13ቱ በላሊጋው ያስቆጠራቸው ናቸው። ከክለብ ወጣ ስንል የተጫዋቹን የብሔራዊ ቡድን ቆይታ እናገኛለን። ዲያዝ በታዳጊነቱ በተለያዩ የእድሜ እርከኖች ለስፔን ወጣት ቡድኖች ተጫውቷል። እ.አ.አ በ2016/17 የውድድር ዘመን ለስፔን ከ17 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን በ16 ዓመቱ ተሰልፎ መጫወት ችሏል። በተለይም አዘርባጃን እ.አ.አ በ2017 ባዘጋጀችው 15ኛው የአውሮፓ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ላይ ያሳየው ድንቅ ብቃት አድናቆት አስችሮታል። በዚያ ቀጥለው በነበሩ ዓመታትም ለስፔን ከ19 እና ከ21 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድኖች ተጫውቷል። ብራሂም ዲያዝ በስፔን ታዳጊና ወጣት ቡድኖች ላይ በአጠቃላይ 28 ጨዋታዎችን አድርጎ ስድስት ግቦችን አስቆጥሯል። የስፔን ታዋቂ የስፖርት ጋዜጣ ማርካ እ.አ.አ ጥር 23 ቀን 2023 ለሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን መጫወት ማቀዱን የሚመለከት ዘገባ ይዞ ወጥቷል። ከዜግነቱ ጋር በተያያዘ ያሉ አንዳንድ የአስተደዳር ጉዳዮች በወቅቱ መፍትሄ አግኝተዋል። ይሁንና ኮትዲቯር እ.አ.አ በ2023 ባዘጋጀችው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሞሮኮው አሰልጣኝ ዋሊድ ሬግራጉዊ ከተጫዋቹ ጋር በተደረገ የቅድሚያ ስምምነት ለተጫዋቹ ጥሪ አልተደረገለትም። ዲያዝ እ.አ.አ መጋቢት 10 ቀን 2024 ለሞሮኮ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለሀገሪቷ ብሔራዊ መጫወት እንደሚፈልግ በይፋ ማሳወቁን ማርካ በወቅቱ ዘግቧል። ጥያቄውም ተቀባይነት አገኘ። በወቅቱ የሞሮኮ አሰልጣኝ ዋሊድ ሬግራጉዊ ብሔራዊ ቡድኑ ከአንጎላ እና ሞሪታኒያ ጋር ለነበረበት የወዳጅነት ጨዋታ ለዲያዝ ጥሪ አድርገውለታል። እ.አ.አ መጋቢት 22 ቀን 2024 ሞሮኮ አንጎላን 1 ለ 0 ባሸነፈችበት ጨዋታ ለብሔራዊ ቡድኑ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። እ.አ.አ ጥቅምት 6 ቀን 2024 ሞሮኮ ለ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከጋቦን ጋር ባደረገችው ጨዋታ 4 ለ 1 ስታሸንፍ የመጀመሪያ ግቡን ለሞሮኮ ማስቆጠር ቻለ። እ.አ.አ ሕዳር 15 ቀን 2024 ሞሮኮ በማጣሪያው ጋቦንን 5 ለ 1 ስትረታ ሁለት ግቦችን ከመረብ ላይ ማሳረፍ ችሏል። ከሶስት ቀናት በኋላ ሞሮኮ ከሌሴቶ ጋር ባደረገችው የአፍሪካ ዋንጫ የመጨረሻ የማጣሪያ ጨዋታ 7 ለ 0 ስታሸንፍ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር በሀገሩ ማልያ የመጀመሪያ ሀትሪኩን ሰርቷል። እ.አ.አ ጥቅምት 2025 ሞሮኮ ራባት ላይ ኮንጎ ሪፐብሊክን 1 ለ 0 በማሸነፍ በስፔን ከዚህ ቀደም በብሔራዊ ቡድን ደረጃ ተይዞ የነበረውን 15 ተከታታይ ጨዋታዎችን የማሸነፍ ክብረ ወሰን በመስበር ወደ 16 ማድረስ ችላለች። በዚህ ታሪካዊ ጨዋታ ላይ ዲያዝ ተሰልፎ ተጫውቷል። የሞሮኮ ተከታታይ የማሸነፍ ጉዞ 19 ጨዋታዎች ደርሶ የነበረ ሲሆን በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ከማሊ ጋር አንድ አቻ ስትለያይ አብቅቷል። ሞሮኮ ለ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በማጣሪያ ብታልፍም አስቀድማ ውድድሩን እንድታዘጋጅ እድል አግኝታ የነበረው ጊኒ በዝግጅት ማነስ ምክንያት በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) ከሁለት ዓመት በፊት አዘጋጅነቷ ተነጥቆ ለሞሮኮ ተሰጥቷል። ሞሮኮ የዘንድሮውን ውድድር በደማቅ ሁኔታ እያካሄደች ትገኛለች። በውድድሩ ላይ ጎልተው ከታዩ ተጫዋቾች መካከል ብራሂም ዲያዝ ተጠቃሽ ነው። በአፍሪካ ዋንጫው እስከ አሁን ባደረጋቸው አምስት ጨዋታዎች አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። በተሰለፈባቸው በእያንዳዱ ጨዋታዎች ጎሎችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ለሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን በአምስት የአፍሪካ ዋንጫ ተከታታይ ጨዋታዎች ግብ ያስቆጠረ የመጀመሪያው ተጫዋች በመሆን አዲስ ታሪክ ጽፏል። ሞሮኮ በሩብ ፍጻሜው ማሊን 2 ለ 0 ስታሸንፍ የመጀመሪያውን ጎል አስቆጥሯል። ሀገሩ ወደ ግማሽ ፍጻሜ እንድታልፍ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱንም እየመራ ይገኛል። ሞሮኮ በዚሁ ግስጋሴዋ ከቀጠለች ዲያዝ የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ እና ኮከብ ተጫዋች የመሆን እድሉ ሰፊ ነው። ሞሮኮ በግማሽ ፍጻሜው ከናይጄሪያ ጋር ረቡዕ ጥር 6 ቀን 2018 ዓ.ም በፕሪንስ ሙላይ አብደላ ስታዲየም ታደርጋለች። ዲያዝ በዚህ ጨዋታ ላይ ልዩነት ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል። አንዳንድ የእግር ኳስ ተንታኞች ብራሂም ዲያዝ እ.አ.አ በ2026 ወጥነት ያለው ብቃት ማሳየት ከቻለ የአፍሪካ ኮከብ ተጫዋችነት ሽልማቱን የሚወስድበት የለም እያሉ ይገኛሉ። ሞሮኳውያን በተጫዋቹ ፍቅር ልባቸው ከንፏል። በየጨዋታው ዲያዝ ዲያዝ እያሉ ከፍተኛ ድጋፍ እና ሙገሳ እየሰጡት ይገኛሉ። እሱም በድንቅ ብቃቱ ምላሽ እየሰጣቸው ነው። በተወለደበት ማላጋ ከተማ የጀመረው የእግር ኳስ ሕይወት በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የበለጠ አብቧል። የሞሮኮው አዲሱ ኮከብ ብራሂም ዲያዝ ቀጣይ የእግር ኳስ ሕይወት በስኬት እና በድል የደመቀ እንደሚሆን ከአሁኑ ድንቅ ብቃቱ ተነስቶ መናገር ይቻላል።
አማድ ዲያሎ - የአፍሪካ እግር ኳስ ብሩህ ተስፋ
Jan 9, 2026 354
ተጫዋቹ አዲሱ ሳሙኤል ኤቶ የሚል ስያሜ እየተሰጠው ይገኛል። ፍጥነቱን ከዲዲየር ድሮግባ ጋር ያነጻጽሩታል። ለተጋጣሚ ተጫዋቾች የራስ ምታት እና ፈተና የሆነውን ግራ እግሩን ከሌላኛው የግራ እግር ምትሃተኛ ሪያድ ማህሬዝ ጋር የሚያወዳድሩም አልጠፉም። በዚህ አካሄዱ ከቀጠለ ያለ ምንም ጥርጥር ወደፊት በእግር ኳስ ከምንመለከታቸው ኮከቦች አንዱ ሊሆን ይችላል እየተባለለት ይገኛል። ይህ ተጫዋች በማንችስተር ዩናይትድ የ147 ዓመታት ታሪክ ሀትሪክ የሰራ የመጀመሪያው አፍሪካዊ ተጫዋች ነው። እያወራን የምንገኘው የማንችስተር ዩናይትድ 16 ቁጥር ማልያ ለባሽ አማድ ዲያሎ ነው። የ23 ዓመቱ ኮትዲቯራዊ ተስፈኛ ተጫዋች በቀያዮቹ ሴጣኖች እያሳየ ያለው ብቃት ከብዙዎች ዘንድ ሙገሳ አስችሮታል፣ አድናቆት እንዲጎርፍለት አድርጓል። ወደ ኋላ መለስ እንበልና የአማድ ዲያሎን መነሻ እንመልከት። ካሜሮን ከአዘጋጇ ሞሮኮ ለግማሽ ፍጻሜ ለማለፍ የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው አማድ የተወለደው እ.አ.አ ጁላይ 11 2002 በኮትዲቭዋር መዲና አቢጃን ነው። ተጫዋቹ በአፍሪካ ምድር ቢወለድም ገና በህጻንነት እድሜው ነበር ወደ ጣልያን የተሰደደው። የእግር ኳስ ህይወቱን የጀመረው እ.አ.አ በ2014 በጣልያን ሬጂዮ ኢሚሊያ ግዛት በሚገኘው ቦካ ባርኮ የታዳጊ ቡድን ነው። ቡድኑን በተቀላቀለበት ዓመት የገና በዓል (ክሪስማስን) በማስመልከት በተካሄደ ውድድር ላይ በ12 ዓመቱ ኮከብ ግብ አግቢ ሲሆን ያሳየው አስደማሚ ብቃት የብዙዎችን ቀልብ ሳበ። ይህ የገና በዓል ውድድር አማድን እ.አ.አ በ2015 በቦካ ባርኮ ቡድን እንዲመዘገብ አደረገው። ተጫዋቹ በቡድኑ ብዙም አልቆየም። የበርካታ የጣልያን ሴሪአ ክለቦች አይን አረፈበት። ብዙም ሳይቆይ በዛው በ2015 ወደ ጣልያኑ አትላንታ አመራ። አማድ ከእ.አ.አ 2015 እስከ 2019 ለአትላንታ ታዳጊ ቡድን የተጫወተ ሲሆን እ.አ.አ 2019 እና 20 ለዋናው ቡድን ተጫውቷል። ለዋናው ቡድን አራት ጨዋታዎችን አድርጎ ማስቆጠር የቻለው አንድ ግብ ብቻ ነው። የእንግሊዙ ክለብ ማንችስተር ዩናይትድ ተጫዋቹ በጣልያኑ ክለብ ባሳየው ብቃት በ18 ዓመት እድሜው እ.አ.አ ጃንዋሪ ወር 2021 በአምስት ዓመት ኮንትራት በ37 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዩሮ አስፈርሞታል። ተጫዋቹ ወደ ማንችተር ሲመጣ ቀጥታ ወደ ዋናው ቡድኑ አልተቀላቀለም። በቡድኑ ከ23 ዓመት በታች ጨዋታውን ማድረግ ጀመረ። አማድ የመጀመሪያ ጨዋታውን ለማንችስተር ያደረገው እ.አ.አ ፌብሩዋሪ 18 2021 ቡድኑ ከሪያል ሶሲዬዳድ ጋር ባደረገው የዩሮፓ ሊግ ጨዋታ ነው። በዛው ዓመት በእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ እና አውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ላይ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ዲያሎ ከእ.አ.አ 2022-2023 ባለው ጊዜ ሬንጀርስ እና ሰንደርላንድ በውሰት የተጫወተ ሲሆን በቡድኖቹ ባደረጋቸው 47 ጨዋታዎች 16 ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። እ.አ.አ በ2023/24 አማድ ወደ ማንችስተር ዩናይትድ በመመለስ በድጋሚ መጫወት ጀምሯል። በክለቡም ድንቅ ብቃቱን እያሳየ መምጣት ጀመረ። እ.አ.አ ጥር 17 2025 ማንችስተር ዩናይትድ ከሊጉ ከወረደው ሳውዝሃምፐን ጋር በነበረው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መርሃ ግብር በ12 ደቂቃ ውስጥ ሶስት ግቦችን አስቆጥሮ ሀትሪክ በመስራት ቡድኑ 3 ለ 1 አንዲያሸንፍ ያደረገበት መንገድ አድናቆት አስችሮታል። በዚህም አማድ በማንችስተር ዩናይትድ የ147 ታሪክ የመጀመሪያ ሀትሪክ የሰራ አፍሪካ ተጫዋች በመሆን አዲስ ታሪክ ጽፏል። አማድ በቀያዮቹ ሴጣኖች ማልያ እስከ አሁን ባደረጋቸው 53 ጨዋታዎች 11 ግቦችን አስቆጥሯል። ተጫዋቹ ከክለቡ በተጨማሪ ለኮትዲቯር ብሄራዊ ቡድን በመጫወት ላይ ይገኛል። እ.አ.አ 2021 ኮትዲቯር ከኒጀር ጋር ባደረገችው ጨዋታ በ86ኛው ደቂቃ ተቀይሮ በመግባት ለብሄራዊ ቡድኑ የመጀመሪያ ጨዋታውን አድርጓል። ለሀገሩ እስከ አሁን ባደረጋቸው 15 ጨዋታዎች አምስት ግቦችን አስቆጥሯል። የመጀመሪያ ጎሉን ኮትዲቯር በ2021 በወዳጅነት ጨዋታ ቡርኪናፋሶን 2 ለ 1 ስታሸነፍ ነበር ያስቆጠረው። አማድ ዲያሎ ዘንድሮ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ድንቅ ጊዜ እያሳለፈ ይገኛል። አማድ በውድድሩ ላይ ባደረጋቸው አራት ጨዋታዎች ሶስት ግቦችን ያስቆጠረ ሲሆን አንድ ለግብ የሚሆን ግብ አመቻችቶ አቀብሏል። ኮትዲቯር ከሞዛምቢክ፣ ካሜሮን እና ቡርኪናፋሶ ጋር ባደረገቻቸው ጨዋታዎች የጨዋታው ኮከብ ሆኖ ተምርጧል። የወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫ አሸናፊ ኮትዲቯር ሩብ ፍጻሜ እንድትደርስ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል። ኮትዲቯር ከግብጽ በሩብ ፍጻሜው ነገ ከግብጽ ጋር ምሽት አራት ሰዓት ላይ በአጋዲር ስታዲየም የምታደርገው ጨዋታ በጉጉጉት ይጠበቃል። ሀገሩ በጠዋታው ላይ ከአማድ ብዙ ትጠብቃለች። ወደ ክለብ እንቅስቃሴው ስንመለስ አማድ በማንችስተር ዩናይትድ ስብስብ ውስጥ ቁልፍ የሚባል ተጫዋች ነው። ፈጣን ኳስን የማንከበላል ክህሎቱ፣ ፍጥነቱ ፣ የቴክኒክ አቅሙ፣ ጨዋታን የማንበብ ብቃቱ እና ሁለቱንም እግሩን የመጠቀም አቅሙ አልፎም ተጫዋቾችን በቄንጥ የሚያልፍበት መንገድ ተጫዋቹን እያስወደሰው ነው። አማድ ዲያሎ ከክንፍ ተጫዋችነቱ ባሻገር የአጥቂ አማካይ ሆኖ መጫወትም ይችላል። እ.አ.አ በ2020 የ18 ዓመት ልደቱን ተከትሎ ተጫዋቹ ስሙን ከአማድ ትራኦሬ ወደ አማድ ዲያሎ አስቀይሯል። አማድ ካለው ድንቅ ብቃት አንጻር ወደፊት በክለብ እና ብሄራዊ ቡድን ደረጃ ድንቅ ጊዜን ካሳለፉ ታዋቂ የአፍሪካ ተጫዋቾች ተርታ የመሰለፉ ጉዳይ አያጠራጥርም።
በ35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ብዙ ለጎል የሚሆኑ ኳሶችን ያቀበሉ ተጫዋቾች
Jan 5, 2026 328
በእግር ኳስ ጨዋታ ከግብ አስቆጣሪዎች ጀርባ ኳስን ፍትፍት አርገው ጨርሰው የሚያቀብሉ ተጫዋቾች አሉ። አንድ ተጫዋች ግብ ሲያገባ ከማግባቱ ባልተናነሰ ማን ኳሱን አቀበለው? የሚለው ጥያቄ በተመልካቾች ይነሳል። በእግር ኳስ እድገት ውስጥ በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ለጎል ኳስ አመቻችተው የሚያቀብሉ ተጫዋቾች ትልቅ ዋጋ ይሰጣቸዋል። ማንችስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ሩበን አሞሪምን አሰናበተ በሞሮኮ አስተናጋጅነት እየተካሄደ በሚገኘው 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች እየተካሄዱ ይገኛሉ። የ33 ዓመቱ የሴኔጋል አምበል ሳዲዮ ማኔ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ካስቆጠረው አንድ ግብ በተጨማሪ ሶስት ለግብ የሚሆኑ ኳሶችን በማቀበል የቀዳሚነቱን ስፍራ ይዟል። ማኔ ሴኔጋል ለሩብ ፍጻሜ እንድታልፍ ያበረከተው አስተዋጽኦ ትልቅ የሚባል ነው። ስምንት ተጫዋቾች በተመሳሳይ ሁለት ለግብ የሚሆኑ ግቦችን አመቻችተው አቀብለዋል። ናይጄሪያውያኑ አዴሞላ ሉክማን እና አሌክስ ኢዎቢ፣ የሞሮኮው አዝዲን ኡናሂ፣ የአልጄሪያው አኒስ ሃጂ-ሙሳ፣ የቡርኪናፋሶው ዳንጎ ኡታራ፣ የቱኒዚያው ሃኒባል ሜጅብሪ፣ የደቡብ አፍሪካው ላይል ፎስተር እና የታንዛንያ ኖቫቱስ ሞሮሺ በሁለት ግቦች ላይ እጃቸው ያለበት ተጫዋቾች ናቸው። የናይጄሪያው የክንፍ የመስመር ተጫዋች አዴሞላ ሉክማን ሁለት ግቦችን በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ አስቆጥሯል። የኮትዲቯሩ ክርስቶፈር ኦፔሪ እና የናይጄሪያው ሳሙኤል ቹኩዌዜ በተመሳሳይ አንድ አንድ ግቦች ከመረብ ላይ እንዲቆጠሩ የቀጥታ ተሳትፎ አድርገዋል። የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬን (ካፍ) የዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ ኮከብ ተጫዋች ምርጫ ላይ ካስቀመጣቸው መመዘኛ መስፈርቶች አንዱ ማን ብዙ ለጎል የሚሆን አቀበለ? የሚለው ይገኝበታል። 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እስከ ጥር 10 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን የግብ አግቢዎችና የኳስ አቀባዮቹ ፉክክር በያዘው ግለት ይቀጥላል ተብሎ ይጠበቃል።
ወንድማማቾች በአፍሪካ ዋንጫ
Dec 29, 2025 452
የአፍሪካ ዋንጫ መልከ ብዙ ውድድር ነው። የሀገራት ተቀናቃኝነት፣ ታሪካዊ ገድሎች፣ አይረሴ የተጫዋቾች የግል ብቃት፣ ጨዋታ ወሳኝ ግቦች እና ዋንጫን ከፍ አድርጎ የማንሳት የኩራት እና የሀገር ፍቅር ስሜት መገለጫዎቹ ናቸው። ከሚቆጠሩ ግቦች እና ዋንጫዎች ባለፈ ቤተሰባዊ ገጽታ ያለው ነው። የአፍሪካ ዋንጫ በርካታ ወንድማማች ተጫዋቾች በአንድ ሀገር ማልያ ሲጫወቱ የተመለከትንባቸው አጋጣሚዎች በርካታ ናቸው። በአህጉራዊው መድረክ የ68 ዓመታት ጉዞ አብረው የተጫወቱ ወንድማቾች በዚሁ ጽሁፍ እንመለከታለን። 1. ኢታሎ እና ሉቺያኖ ቫሳሎ (ኢትዮጵያ) ኢታሎ ቫሳሎ እና ሉቺያኖ ቫሳሎ በአፍሪካ ዋንጫ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጫወቱ ወንድማማቾች መሆናቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን መረጃ ያመለክታል። ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ1962 ባዘጋጀችው ሶስተኛው የአፍሪካ ዋንጫ የቫሳሎ ወንድማማቾች አንድ ላይ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጫውተዋል። ሉቺያኖ በውድድሩ ላይ ሶስት ግቦችን በማስቆጠር ከግብጹ ባደዊ አብድል ፈታህ ጋር በጋራ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኖ አጠናቋል። ሉቺያኖ የውድድሩ ኮከብ ተጫዋች ተብሎ የተመረጠ ሲሆን ይህም በውድድሩ ታሪክ የኮከብ ተጫዋችነትን ሽልማት ያገኘ የመጀመሪያው ተጫዋች እንዲሆን አስችሎታል። ኢትዮጵያ በወቅቱ የአፍሪካ ዋንጫን ማንሳቷ የሚታወስ ነው። 2. ሆሳም እና ኢብራሂም ሀሰን (ግብጽ) ሆሳም ሀሰን እና ኢብራሂም ሀሰን በአፍሪካ ዋንጫው ስኬታማ የሚባሉ ወንድማማች ተጫዋቾች ናቸው። እ.አ.አ በ1986 ግብጽ ያስተናገደችውን 15ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና እ.አ.አ በ1998 በቡርኪናፋሶ የተካሄደውን 21ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ግብጽ ስታነሳ የቡድኑ አባላት ነበሩ። ወንድማማቾቹ የአፍሪካ ዋንጫን ሁለት ጊዜ በማንሳት ባለ ክብረ ወሰን ናቸው። የ59 ዓመቱ ሆሳም ሀሰን በአሁኑ ሰዓት የግብጽ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ነው። በተጫዋችነቱ በ177 ጨዋታዎች 69 ግቦችን ከመረብ ላይ በማሳረፍ የምንጊዜውም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ነው። 3. አልበርት ባዋንጋ እና ሮበርት ካዛዲ (ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ) ሁለቱ ወንድማማቾች ግብጽ እ.አ.አ በ1974 ባዘጋጀችው ዘጠነኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። በወቅቱ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ዛምቢያን በማሸነፍ ዋንጫውን ስታነሳ የታሪካዊው ድል አካል ነበሩ። 4. አንድሬ ካና ቢይክ እና ፍራንስዋ ኦማም ቢይክ (ካሜሮን) ሁለቱ ወንድማማቾች በሶስት የአፍሪካ ውድድሮች ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። ተጨዋቾቹ ለመጀመሪያ ጊዜ በአህጉራዊ መድረክ በጋራ የመሰለፍ እድል ያገኙት እ.አ.አ በ1988 በሞሮኮ አስተናጋጅነት በተካሄደው 16ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ነው። እ.አ.አ በ1990 በአልጄሪያ በተካሄደው 17ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ሴኔጋል እ.አ.አ በ1992 ባዘጋጀችው 18ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በጋራ ተሰልፈዋል። ጣልያን እ.አ.አ በ1990 ባዘጋጀችው 14ኛው የዓለም ዋንጫ ከወንድማማቾቹ ታናሹ ፍራንስዋ ኦማም ቢይክ ካሜሮን አርጀንቲናን 1 ለ 0 ባሸነፈችበት ጨዋታ ባስቆጠራት ጎል ሁሌም በሀገሬው ሰዎች ሲወሳ ይኖራል። 5. አንድሬ አየው እና ጆርዳን አየው (ጋና) ጋናውያኑ ወንድማሞች የአፍሪካ ዋንጫ ሲነሳ ሁሌም የሚታወሱ ተጫዋቾች ናቸው። በስድስት የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ አብረው ተሰልፈዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ አብረው የሰለፉት ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን እ.አ.አ በ2012 ባዘጋጁት 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። የአየው ወንድማማቾች እ.አ.አ በ2015 ኢኳቶሪያል ጊኒ ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለማንሳት ተቃርበው የነበሩ ቢሆንም በፍጻሜው በኮትዲቭዋር በመለያ ምት ተሸንፈው ህልማቸው ሳይሳካ ቀርቷል። የታዋቂው አፍሪካዊ ተጫዋች አብዲ ፔሌ ልጆች የሆኑት አንድሬ እና ጆርዳን አየው እ.አ.አ በ2023 በኮትዲቭዋር አስተናጋጅነት በተካሄደው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ለመጨረሻ ጊዜ በጋራ ተሰልፈዋል። ጋና እ.አ.አ በ2008 ባዘጋጀችው 26ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጋናዊው አጥቂ አሳሞሃ ጊያን እና ታናሽ ወንድሙ ባፎር አንድ ላይ ተጫውተዋል። በተጨማሪም በዛው ውድድር ላይ ጋናውያኑ ወንድማማቾች ሪቻርድ ኪንግስተን እና ላሪያ ጊንግስተን አብረው የመጫወት እድል አግኝተዋል። 6. ኮሎ ቱሬ እና ያያ ቱሬ (ኮትዲቭዋር) በአፍሪካ እግር ኳስ ውስጥ ስማቸው በግንባር ቀደምትነት ከሚነሱ ተጫዋቾች መካከል ኮሎ ቱሬ እና ያያ ቱሬ ይጠቀሳሉ። ወንድማማቾቹ ለመጀመሪያ ጊዜ አብረው የተሰለፉት እ.አ.አ በ2006 በግብጽ አስተናጋጅነት በተካሄደው 25ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ነው። በወቅቱ ኮትዲቭዋር ለፍጻሜ ደርሳ በግብጽ ተሸንፋለች። ኢኳቶሪያል ጊኒ እ.አ.አ በ2015 ባዘጋጀችው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ኮትዲቭዋር ጋናን በማሸነፍ ዋንጫውን ለሁለተኛ ጊዜ ስታነሳ በጋራ የድሉ ተቋዳሽ ሆነዋል። የቱሬ ወንድማማቾች ለስድስት ጊዜ በአፍሪካ ዋንጫው አብረው ተጫውተዋል። 7. የሞሪታኒያ እና ዛምቢያ ወንድማማች ተጫዋቾች እ.አ.አ በ2023 ኮትዲቭዋር ባስተናገደችው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሞሪታኒያ ብሄራዊ ቡድን ስብስብ ከሁለት ቤተሰብ በተመሳሳይ ሁለት ወንድማማቾች መሳተፋቸው የተለየ ትኩረት ስቧል። ኑህ መሐመድ አብድ እና ታናሹ ሲዲ መሐመድ አህመድ አብድ በተከላካይ እና አማካይ መስመር ላይ ተሰልፈው ተጫውተዋል። ላሚን ባ እና ኤል ሃጂ ባ ለሞሪታኒያ ብሄራዊ ቡድን በመሰለፍ መጫወት ችለዋል። ዛምቢያዊያኑ ክርስቶፈር እና ፍሊክስ ካቶንጎ እ.አ.አ በ2012 ኢኳቶሪያል ጊኒ እና ጋቦን በጣምራ ባዘጋጁት 28ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ዛምቢያ ኮትዲቭዋር በማሸነፍ የአፍሪካ ዋንጫን ስታነሳ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል። ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ2013 ባዘጋጀችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይም በጋራ ተሰልፈው ተጫውተዋል። ዛምቢያውያኑ ወንድማማቾች ኬኔት እና ሞርዶን ማሊቶሊ እ.አ.አ በ1994 በቱኒዚያ በተካሄደው 19ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ1996 ባዘጋጀችው 20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አንድ ላይ ተሰልፈዋል። አለን ትራኦሬ እና ኢብራሂማ ትራኦሬ (ቡርኪናፋሶ) በ30ኛው እና 31ኛው የአፍሪካ ፣ ሳምቡ ያታባሬ እና ሙስጠፋ ያታባሬ (ማሊ) በተመሳሳይ በ30ኛው እና 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ፒተር ንዶልቩ እና አዳም ንዶልቩ (ዚምባቡዌ) በ24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ሳሉ፣ ባቺሩ እና ታጁ (ቶጎ) በ22ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ ቾሞጎ ኦማር እና ሴዲያት ኦማር (ቤኒን) በ24ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፣ መሐመድ እና ሙሳ ካሎን (ሴራሊዮን) በ20ኛው የአፍሪካ ዋንጫ እና ሳሚር ሳሊሚና አዴል ሳሊሚ (ቱኒዚያ) በ19ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አብረው የተሰለፉ ተጫዋቾች ናቸው። በአፍሪካ ዋንጫ ከተሰለፉ ወንድማማቾች መካከል ስድስቱ የአፍሪካ ዋንጫን ማንሳታቸውን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) አስታውቋል።
የኢትዮጵያ እና የህንድ ዘመን አይሽሬ እና ድንበር ተሻጋሪ ወዳጅነት
Dec 16, 2025 753
በሙሴ መለስ (ኢዜአ) ኢትዮጵያ እና ህንድ ረጅም ክፍለ ዘመናትን ያስቆጠረ ወዳጅነት እና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት አላቸው። በዚህም የስልጣኔ እሴቶችን ይጋራሉ። ሁለቱ ሀገራት የንግድ ትስስር ከፈጠሩ ከ2000 ዓመታት በላይ እንዳስቆጠሩ የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ። የኢትዮጵያ እና ህንድ ዘመናዊ የዲፕሎማሲ ግንኙነት መሰረት የሀገራቱ ታሪካዊ ወዳሽነት እንደሆነም ይወሳል። ኢትዮጵያ እና ህንድ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1948 ነው። እ.አ.አ በ1950 ሳርዳት ሳንት ሲንግ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የህንድ አምባሳደር በመሆን ተሹመዋል። በወቅቱ ኢትዮጵያ እና ህንድ በየሀገራቱ ኤምባሲ በመክፈት የዲፕሎማሲ ትብብሩን ለማጠናከር ያላቸውን ቁርጠኝነት በተግባር ገልጸዋል። ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ እ.አ.አ በ1956 እና በ1958 በህንድ ያደረጓቸው ጉብኝቶች ከኢትዮጵያ መሪዎች ጉብኝቶች በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው። እ.አ.አ 1960 ዎቹ ማብቂያ እና 1970ዎቹ መጀመሪያ ላይ የህንድ ፕሬዝዳንቶች የነበሩት ሳርቬፓሊ ራድሃክሪሽናን እና ዛኪር ሁሴን በኢትዮጵያ የስራ ጉብኝቶችን አድርገዋል። እ.አ.አ በ2011 ከአንድ ዓመት በፊት ህይታቸው ያለፈው የቀድሞው የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ማንሞሃን ሲንግ በኢትዮጵያ ያደረጉት የስራ ጉብኝትም ተጠቃሽ ነው። የቀድሞው የህንድ ፕሬዝዳንት ራም ናት ኮቪንድ እ.አ.አ በ2017 የስራ ጉብኝት ያደረጉ ሲሆን በወቅቱ በጉብኝታቸው ህንድ እና ኢትዮጵያ በንግድ፣ ኮሙኒኬሽን እና የሁለትዮሽ ትብብር ማጠናከር የሚያስችሉ የጋራ መግባቢያ ስምምነቶችን ተፈራርመዋል። ደቡብ አፍሪካ እ.አ.አ በ2023 ባዘጋጀችው 15ኛው የብሪክስ የመሪዎች ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከነበራቸው ተሳትፎ ጎን ለጎን ከህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አድርገዋል። የሀገራቱ መሪዎች በወቅቱ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በመከላከያ፣ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በግብርና፣ የወጣቶች ክህሎት ማጎልበት እና በሕዝብ ለሕዝብ ልውውጥ ዙሪያ ትብብርን በማጠናከር ዙሪያ ተወያይተዋል። በወቅቱ ህንድ ባዘጋጀችው የሁለተኛው “Voice of Global South Summit” በተሰኘው ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ተሳትፎ አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ2016 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንደራ ሞዲ በህንድ አጠቃላይ ምርጫ ለሶስተኛ ጊዜ ማሸነፋቸውን ተከትሎ የእንኳን ደስ አለዎት መልዕክት አስተላልፈውም ነበር። የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንደራ ሞዲም የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)ን የደስታ መግለጫ መልዕክት በመቀበል በአዲሱ የስልጣን ዘመናቸው ህንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት አጋርነት እንደሚያድግ መግለጻቸውም ይታወሳል። ህንድ እና ኢትዮጵያ በአፍሪካና በደቡብ ደቡብ ትብብር ያላቸውን አጋርነት ጠቅላይ ሚኒስትሩ አንስተዋል። በዚህም ህንድ ከኢትዮጵያ ጋር ላላት የሁለትዮሽ ትብብር ከፍተኛ ትኩረት እንደምትሰጥም ነበር ጠቅላይ ሚኒስትር ሞዲ ያስታወቁት። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው 20ኛው የቡድን 20 አባላት ሀገራት ጉባኤ ከነበራቸው ተሳትፎ ጎን ለጎን ከህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ጋር ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ከህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ትርጉም ያለው እና ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውንም ገልጸዋል። ህንድ የቡድን 20 አባል ሀገር መሆኗ የሀገራቱን የባለብዙ ወገን ትብብር የበለጠ የሚያጠናክር ነው። ከእ.አ.አ 2021 እስከ 2024 ባለው ጊዜ ውስጥ ሀገራቱ የሁለትዮሽ እና የባለዙወገን ትብብራቸውን የሚያጠናክሩ ተከታታይ ውይይቶችን አድርገዋል። በወቅቱ የህንድ የትምህርት፣ ንግድ፣ ልማት፣ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሮች በኢትዮጵያ ያደረጓቸው ጉብኝቶች የሀገራቱ ግንኙነት የበለጠ እየጠነከረ መምጣቱን የሚያሳዩ ናቸው። ህንድ ኢትዮጵያ የብሪክስ አባል እንድትሆን ድጋፍ ያደረገች ሲሆን በብዝሃ ወገን ማዕቀፉ ሁለቱ ሀገራት በትብብር እየሰሩም ይገኛሉ። ኢትዮጵያ እና ህንድ በተለያዩ ጊዜያት በአየር ትራንስፖርት፣ ኢኮኖሚ፣ ኢንቨስትመንት፣ መከላከያ፣ ተደራራቢ ታክስን የማስቀረት፣ ንግድ፣ ኮሙኒኬሽን ሳይንስ፣ባህል፣ ትምህርት እና የጋራ ሚኒስትሮች ኮሚሽን ማቋቋምን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች መስራት የሚያስችሏቸው የሁለትዮሽ ስምምነቶችን ተፈራርመዋል። እ.አ.አ ፌብሩዋሪ 2025 ኢትዮጵያ እና ህንድ በመከላከያና ደህንነት ዘርፍ የተፈራረሙት የሁለትዮሽ ስምምነት ቁልፍ የሚባል ነው። እ.አ.አ በ2023/24 በወጣ መረጃ የኢትዮጵያ እና ህንድ የሁለትዮሽ የንግድ ልውውጥ ምጣኔ 271 ሚሊዮን ዶላር ደርሷል። ኢትዮጵያ አተር፣ ቅመማ ቅመሞች፣ የቆዳ ውጤቶች እና የከበሩ ድንጋዮችን ወደ ህንድ ትልካለች። ከህንድ ደግሞ ማሽነሪዎች፣ የመድኃኒትት ምርቶች እና የብረታ ብረት ውጤቶችን በዋናነት ታስገባለች። ህንድ የኢትዮጵያ ዋንኛ የኢንቨስትመንት አጋር ከሚባሉ ሀገራት መካከል ትጠቀሳለች። ከ500 በላይ የህንድ ኩባንያዎች በጨርቃ ጨርቅ፣ ግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግ እና አገልግሎት ዘርፎች ተሰማርተው ይገኛሉ። ህንድ መሰረተ ልማቶችን ጨምሮ ለኢትዮጵያ ግዙፍ ፕሮጀክቶች የፋይናንስ አቅርቦት ታደርጋለች። ንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ትምህርት፣ ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂ፣ ኢኖቬሽን፣ ጤና እና መሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ከሁለቱ ሀገራት አበይት የትብብር መስኮች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው። የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ በኢትዮጵያ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ለማድረግ ዛሬ ማምሻውን አዲስ አበባ ገብተዋል። ሞዲ በኢትዮጵያ ጉብኝት ሲያደርጉ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ከማንሞሃን ሲንግ በኋላ ኢትዮጵያን የጎበኙ ሁለተኛው ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት ህንድ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከአፍሪካ ጋር ያላትን የልማት አጋርነት ማሳደግን ያለመ ነው። የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ በኢትዮጵያ ቆይታቸው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጨምሮ ከሌሎች የመንግስት ባለስልጣናት ጋር ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አባላት በፓርላማ ተገኝተው ንግግር እንደሚያደርጉ የጉብኝታቸው መርሃ ግብር ያሳያል። የሁለቱ ሀገራት መሪዎች ተከታታይ የሁለትዮሽ ውይይቶች እና የጉብኝት ልውውጦች የኢትዮጵያ እና የህንድን ግንኙነት የበለጠ የሚያጸኑ ናቸው። ኢትዮጵያ እና ህንድ በታዳሽ ኃይል፣ ፋርማሲዩቲካል፣ ዲጂታል ቴክኖሎጂ እና ግብርና ማቀነባበሪያን ጨምሮ በአዳዲስ መስኮች ትብብራቸውን የማጠናከር ጽኑ ፍላጎት አላቸው። የሁለቱ ሀገራት ትብብር ከእርስ በእርስ ግንኙነት ባለፈ የአፍሪካ እና ህንድ እንዲሁም የደቡብ ደቡብ ትብብር ማሳያ ሆኖ የሚጠቀስ ነው። ከ2000 ዓመት በፊት የተጀመረው የሀገራቱ ወዳጅነት ወደ ጠንካራ እና ጽኑ ትብብር ተቀይሯል። በማይናወጥ መሰረት ላይም ቆሟል። የበለጠ ጥልቀቱ እየጨመረ የመጣው የሀገራቱ ግንኙነት በጋራ ብልጽግና፣ ስትራቴጂካዊ ትስስር፣ ዘላቂ ልማት እና የሀገራቱን ዜጎች ተጠቃሚ ባደረገ መልኩ አጠናክሮ ለመቀጠል የጋራ ቁርጠኝነቱ ከመቼውም ጊዜ በላይ ጨምሯል።
በአረንጓዴ ልምላሜ ያጌጠው - የቤንቾች ቀዬ
Dec 3, 2025 1096
በአረንጓዴ ልምላሜ ያጌጠው - የቤንቾች ቀዬ (በቀደሰ ተክሌ) -ከሚዛን ቅርንጫፍ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የሚገኘው የቤንች ምድር የሰጡትን የሚያበቅል ክረምት ከበጋ የማይጠወልግ ልምላሜን የታደለ ክልል ነው። በቤንች ሸኮ ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች ደን የሚመስልና በመኖሪያ መንደሮች የሚታየው አብዛኛው አረንጓዴ ስፍራ ለምግብነት የሚያገለግሉ ፍራፍሬዎች፣ ቅጠሎችና ስሮችን የያዘ ነው። የቤንቾች ቤት ዙሪያው በአረንጓዴ ተፈጥሮ ያጌጠ ነው። የቤታቸው ሞገስ፤ የምግብ ዋስትናቸውም ጭምር ነው። ከዚህ ከፍ ሲል ደግሞ ቤንቾች ነፋሻማ አየር እየማጉ የመኖር ልምድን ያጎናጸፋቸው ይኸው አፈር ቆፍረው ዘር ተክለው ያበቀሉትና የተንከባከቡት አረንጓዴ ሀብት ነው። ከአንድ አርሶ አደር ማሳ እንሰት፣ ሙዝ፣ ጎደሬ፣ ፓፓያ፣ አቮካዶ፣ ብርቱካን እና ሌሎች ፍራፍሬዎች ማየት የተለመደ ነው። እግር ጥሎት ወደ ቀዬያቸው ያመራ እንግዳ ከፍራፍሬዎቹ የደረሰ ካለ ተቆርጦ ይሰጠዋል። በተጨማሪም ከብቶች፣ በጎችና ዶሮዎች የገቢ ምንጮቻቸው ናቸው። ወደ ቤታቸው ዘልቆ የገባ ሰው "ኪዥ" የተሰኘና የቤንች እናቶች ከወተት የሚያዘጋጁትን ''ጎደሬ'' ተብሎ ከሚጠራ የስራ ስር ምግብ ጋር ያጣጥማል። ቤንቾች በቆሎ፣ ማሽላ፣ ስንዴ፣ ባቄላ እንዲሁም ሌሎች የሰብል ዓይነቶችን ያለማሉ። ማር፣ ቡና፣ ኮረሪማ እና ሌሎች የተፈጥሮ ቅመማ ቅመሞችም ቤንቾች ከገበያ ገዝተው የሚያመጡት ሳይሆን ከማሳቸው የሚያፈሩት ነው። የተቀናጀ እርሻን ባህል ያደረጉት ብርቱ የቤንች አርሶ አደሮች ወደ ገበያ አውጥተው የሚሸጡት እንጂ የሚገዙት የለም ቢባል ማጋነን አይሆንም። የፋብሪካ ውጤቶችን ለመግዛትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግም ከጓዳቸው ሞልቶ የተረፈውን ወደ ገበያ አውጥተው በመሸጥ ገበያን ያረጋጋሉ። በጠንካራ የእርሻ ባህላቸውም ምክንያት ልጆቻቸው የበሰለ ምግብን ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ፍራፍሬዎችንም ከጓሮና ከጫካ ቆርጠው ስለሚመገቡ ረሀብን አያውቁም። የቤንቾች ቤት ዙሪያ ውብና ጽዱ ነው። ለዚህ ደግሞ ሴቶቹ የቤታቸውን ግድግዳ በተፈጥሮ ቀለም ከማስዋብ ጀምሮ ይጠበቡበታል። በቤንቾች ዘንድ የአንድ አርሶ አደር ጉብዝና የሚለካው በቤቱ ነው። ይህም የቤቱ ዙሪያ ያለው ውበትና የቤቱ ጥንካሬ ብቻም ሳይሆን ገላጣ መሆን አለመሆኑም ጭምር ከግምት ውስጥ ይገባል። አባዎራው በማሳው ላይ የሰብል ስራውን ያከናውናል። ልጆችና እማውራዋ ደግሞ ይኮተኩታሉ ያርማሉ። ከዚህም በተጨማሪ የቤንች እናት ጎደሬና ሌሎች የጓሮ አትክልቶችን የማልማት ኃላፊነት አለባት። የቤታቸው ዙሪያና ቀዬው በሙሉ በአረንጓዴ ልምላሜ አጊጦ የሚታይበት ምስጢሩ ይሄው ነው። ከርቀት ደን መስሎ የሚታየው አረንጓዴው ቀዬአቸው የገቢ ምንጭም በመሆኑ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ነውም ማለት ይቻላል። የሌማት ትሩፋት እሳቤ ቀድሞ የገባቸው ቤንቾች ማር አይገዙም፤ ለእንቁላል ሸመታም ገበያ አይወጡም። ወተት ቢያምራቸው በትኩሱ፤ ከዛም አለፍ ሲል በባህላዊ መንገድ እርሾ ጨምረው የሚያዘጋጁት "ኪዥ" የተሰኘ የወተት ውጤትን እንደ አይብም እንደ እርጎም አደርገው ይጠቀሙታል። የትኛውንም መልክዓ ምድር በሚስማማው የሰብል ዓይነት መሸፈን ያውቁበታል። መሬቱ ረግረጋማ ከሆነ ለጎደሬ፤ ዳገታማ ሆኖ ለማረስ የሚያስቸግር ከሆነ ደግሞ ለሙዝ ልማት ያውሉታል። የምግብ ዋስትናን በቤተሰብ ደረጃ ለማረጋገጥ ሥራ የሚሠራው በጓሮ ነው። ይህም ሁሉን ከአንድ ጓሮ ለማግኘት በመጣር የሚመጣ ነው። ይህም ካልሆነ ደግሞ አስተማማኝና ቋሚ ምርት ማሳ ላይ አልያም ጎተራው ላይ ማኖር ያስፈልጋል። እንደ ቤንቾች በቤተሰብ ደረጃ ምግብን በራስ አቅም ለመቻል የሚደረገው ጥረት እንደሀገር ሲጠናከር ለውጡ ቀጣይነት ባለው መልኩ ይፋጠናን። ሀገራችን ኢትዮጵያ ካላት የሕዝብ ቁጥር አብዛኛው አርሶ አደር ነው። ይሁን እንጂ ጾሙን የሚያድር ሰፊ መሬት እንዳለ መረጃዎች ያመለከታሉ። አንድም መሬት ጾም እንዳያድር በየአካባቢው ስራዎች ቢጀመረም ውጤቱ ቀሪ ሥራዎችን የሚጠይቅ ነው። ዛሬም በምርት እጥረት የኑሮ ውድነትና መሰል ችግሮች ይስተዋላሉ። በእነዚህ መሬቶች ላይ ሰርቶ ከመለወጥ ይልቅ ከተማ ቁጭ ማለትን የሚሻ ትውልድ ማየት የተለመደ ነው። የቤንች ሸኮ ዞን አርሶ አደሮች እጃቸው ብርቱ በመሆኑ እነዚህ ችግሮች በስራ አሽንፈዋል። ይህም በምግብ ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ በኢኮኖሚም እንዲረጋጉ አድርጓቸዋል። ለሀብት ምንጭ የሆነን ማሳ ለቆ ከተማ በመዋል የሚገኝ ነገር አይኖርም። በከተማም ሆነ በገጠር ለመለወጥ እንደ ቤንቾች ብርቱ እጆች ያስፈልጋሉ። ካልተሰራ ገቢ ሳይሆን ወጪ እያደገ ወዳልተገባ መንገድ ለመሄድ ምክንያት ይሆናል። ለችግርም ሆነ ሰርቶ የመለወጥ ዕድሉ የሚወሰነው በምርጫችንና ለሥራችን በምንሰጠው ትኩረት ነው። እንደ ቤንች ሸኮ ዞን አርሶ አደሮች ሰርቶ ለመለወጥና ራስን ለመቻል በየአካባቢው ያለን የተፈጥሮ ሀብት ወደ ልማት ለመቀየር ተግቶ መስራት ያስፈልጋል ። ሰላም!
ብልህ ከችግር ይማራል!!
Dec 2, 2025 629
ብልህ ከደረሰበት ችግር ይማራል!! በማሙሽ ጋረደው ገራድ ተስፋዬ ተፈራ ትውልድና እድገታቸው በሀድያ ዞን ሌሞ ወረዳ ቃልሻ ቀበሌ ሲሆን በ1999 ዓ.ም በህገ ወጥ መንገድ ከፍተኛ ገንዘብ አውጥተው ወደ ደቡብ አፍሪካ ተጉዘው እንደነበር ያስታውሳሉ። ገንዘብ ለማግኘትና የመለውጥ ህልማቸውን ለማሳካት በሚል ሩቅ አስበው የጀመሩት ህገ ወጥ ጉዞ መዳረሻውን እስር ቤት አደረገው። ይህም ሁኔታ ''ሩቅ አሳቢ-ቅርብ አዳሪ'' አደረጋቸው። በባዕድ አገር በነበራቸው የ2 ዓመት የእስር ቤት ቆይታም የምግብ እጦትን ጨምሮ አካላዊ ጥቃትና ጉልበት ብዝበዛ እንዲሁም የተለያዩ ስነ-ልቦናዊ ጉዳቶችን እንዳስተናገዱ ይናገራሉ። ይህም አልበቃ ብሎ ከአካባቢው በህገወጥ መንገድ የሚሰደዱ ወጣቶችን ጉልበት በመጠቀም ሰፋፊ እርሻዎች ላይ እንዲሰማሩ በማድረግ የጉልበት ብዝበዛ ይፈፀምባቸው እንደነበርም ያስታውሳሉ። ብልህ ከደረሰበት ችግር ይማራል! የሚሉት ገራድ ተስፋዬ ሩቅ ሳይጓዙ፣ ገንዘብ ሳያወጡ ሰርተው መለወጥ የሚችሉበትን አካባቢያቸውን ፀጋ ሳያማትሩ ስደት መሄዳቸው ቁጭት ፈጥሮባቸው ነበር፡፡ ይህም በሀገራቸው እንኳንስ የለማን መሬት ይቅርና የተቦረቦረ መሬትን አልምቶ ጉልበትንና ጊዜን በአግባቡ ተጠቅሞ ለስኬት መብቃት እንደሚቻል ከእስር ቤት ቆይታቸው ተምረው ከእስር እንደተፈቱም ወዲያውኑ ወደ ሀገር ቤት መመለሳቸውን ተናግረዋል። በ2001 ዓ.ም ወደ ሀገር ቤት እንደተመለሱም በማህበር ተደራጅተው ከመንግሥት ባገኙት 70 ሺህ ብር ብድር በእንስሳት እርባታ ላይ ለመሰማራት 4 የወተት ከብቶችን ገዝተው የእርባታ ስራ መጀመራቸውን ይገልጻሉ፡፡ በዚህም የዞኑ አስተዳደር የሰጣቸውን መሬት አልምተው የእንስሳት እርባታውን አስፋፍተው መስራት ጀመሩ፡፡ አሁን ላይ የወተት ላሞቹን ቁጥር 37 በማድረስ የወተት ምርታማነታቸው አድጎ ከቤት ፍጆታ አልፎ ለሆሳዕና ከተማና አካባቢው በቀን ከ670 ሊትር በላይ ወተት እያቀረቡ ይገኛሉ፡፡ ለ40 ወጣቶችም ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል ከመፍጠራቸውም ባሻገር የተለያዩ የጭነትና የስራ ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ ከ250 ሚሊዮን ብር በላይ ሀብት ማፍራት መቻላቸውን ይናገራሉ። የጀመሩትን ስራ በጥምር ግብርና የማስፋትና የሚያገኙትን ወተት በማቀነባበር ምርቱን በተለያየ መልኩ ለገበያ የማቅረብ ራዕይን ሰንቀው በትጋት እየሰሩ ይገኛሉ፡፡ በህገወጥ ስደት ካጋጠማቸው ችግር ተነስተው በተግባር ያዩትን ለሌሎች በማስተማር የስደትን አስከፊነት ለአካባቢያቸው ወጣቶች እያስገነዘቡ መሆኑን ገልጸዋል። ወጣቶች የስደትን አማራጭ ከመመልከታቸው በፊት የአካባቢያቸውን ፀጋ እንዲቃኙና ራዕይ ሰንቀው ራሳቸውን ለማሻሻል እንዲሰሩም መክረዋል። መለወጥ በውጪ ሀገር ብቻ ያለ የሚመስላቸው የቤተሰብ ኃላፊዎችም ልጆቻቸው በሀገራቸው ሰርተው መለወጥ እንደሚችሉ በማመን ሊያግዟቸው እንደሚገባም አቶ ገራድ አስገንዝበዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትልና የእርሻና ሆርቲካልቸር ዘርፍ ኃላፊ አቶ አለምይርጋ ወልደስላሴ፤ በክልሉ በርካታ ወጣቶች ያልተጨበጠ ተስፋ ሰንቀው ለህገወጥ ስደትና ለተለያዩ ችግሮች ተጋላጭ እየሆኑ ይገኛሉ ብለዋል፡፡ በሀገር ሰርቶ ለመለወጥ የሚያስችል አቅም በግብርናው ዘርፍ መኖሩን ጠቅሰው በዘርፉ የተሰማሩ ከስደት ተመላሾች በአካባቢያቸው ሰርተው ለስኬት እየበቁ እንደሚገኙም ጠቁመዋል፡፡ በዚህም ከራሳቸው አልፈው ለበርካታ ስራ አጥ ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር ላይ የሚገኙና የእነዚህን አካላት ተሞክሮ በመውሰድ በሀገር ሰርቶ ለመለወጥ መትጋት ይገባል ብለዋል፡፡
ዲጂታል ግብርና፤ የአፍሪካ ግብርና አዲስ ምዕራፍ
Dec 1, 2025 325
ዲጂታል ግብርና በጥቅሉ ሲተረጎም የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን ለግብርና ስራዎች መጠቀም ማለት ነው። ቴክኖሎጂዎቹ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ፣ የገበያ ተደራሽነትን በማስፋት፣ በአቅርቦት የእሴት ሰንሰለት ላይ መጠናከር፣ በቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት፣ የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምና የአየር ንብረት ለውጥ አይገበገሬነት ስራዎችን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አላቸው። የዓለም የዲጂታል ግብርና ገበያ እ.አ.አ በ2022 ከ10 እስከ 12 ቢሊዮን መድረሱን የተለያዩ መረጃዎች ያመለክታሉ። እ.አ.አ በ2028 የገበያ መጠኑ ከ23 እስከ 25 ቢሊየን ዶላር እንደሚደርስ ትንበያ ተቀምጧል። የዲጂታል ግብርና በአውሮፓ፣ በሰሜን አሜሪካ እና እስያ ፓሲፊክ በፍጥነት እያደገ ሲሆን በአፍሪካና ላቲን አሜሪካ ጅምር ላይ ነው ማለት ይቻላል። ሰሜን አሜሪካ 40 በመቶ እና አውሮፓ 25 በመቶ የዓለም የዲጂታል ግብርና ገበያ ድርሻን ይይዛሉ። አርሶ አደሮች ለዲጂታል ግብርና የሚያስፈልጋቸውን ቴክኖሎጂዎችን አለማግኘት፣ የዳታ ደህንነት እና የግል መረጃ ጥበቃ፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የኢንተርኔት ተደራሽነትና ባህላዊ ልማዶችን ከዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ጋር ማስተሳሰር ዓለም አቀፍ የዘርፉ ፈተናዎች ናቸው። አፍሪካ ከአምስት እስከ ሰባት በመቶ(ከ500 እስከ 800 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር) የሚገመት ነው። በአፍሪካ የግብርና ቴክኖሎጂ ያለው ኢንቨስትመንት በፍጥነት እያደገ ይገኛል። ዘርፉ ከ400 ሚሊየን ዶላር መዋዕለ ንዋይ ፈሶበታል። በሞባይል የማማከር አገልግሎት፣ የገበያ ትስስር ማዕቀፎችና ለአርሶ አደሮች የፋይናንስ ቴክኖሎጂዎች ተደራሽ የማድረግ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። የቴክኖሎጂዎቹ የተደራሽነትና አላምዶ የመጠቀም ውስንነት፣ የመሰረተ ልማት ግንባታ፣ የፖሊሲ እና የህግ ማዕቀፍ እክሎች እንዲሁ አካታችነት የአፍሪካ ፈተናዎች ናቸው። በአፍሪካ አብዛኛው ግብርና በአነስተኛ ይዞታ ባላቸው አርሶ አደሮች ላይ የተመሰረተ ሲሆን ግብርና ለአፍሪካውያን ኑሮ እና የምግብ ዋስትና ወሳኝ የሚባል ነው። በዚህ ረገድም የዲጂታል ግብርና ለግብርና ምርታማነት ማደግ፣ የአቅርቦት እጥረትን በመቅረፍና የልማት ግቦች በማሳካት ረገድ የበኩሉን ሚና ይጫወታል። ኢትዮጵያ ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት በጥር ወር 2017 ዓ.ም የዲጂታል ግብርና ፍኖተ ካርታ ይፋ አድርጋለች። በወቅቱ የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ከግብርና ሚኒስቴር እና የጌትስ ፋውንዴሽን ጋር በመሆን ፍኖተ ካርታውን በጋራ ይፋ አድርገዋል። ማዕቀፉ ከዚህ ቀደም የነበሩ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴንሽንና ማማከር አገልግሎቶች በአንድ ጥላ ስር ያስቀመጠ ነው። ፍኖተ ካርታው የግብርና እሴት ሰንሰለቱን በሙሉ ዲጂታላይዝ የማድረግ አላማ አለው። የማማከርና የፋይናንስ አገልግሎቶች፣ የገበያ መረጃ፣ ዲጂታል ክህሎት፣ ሜካናይዜሽን፣ የዳታ መረጃ አሰባሰብና ዲጂታል መሰረተ ልማት የፍኖተ ካርታው አበይት ትኩረቶች ናቸው። መንግስት ከልማት አጋሮች ጋር በመሆን የዲጂታል ግብርናን ለማስፋት እየሰራ ነው። የአፍሪካ ህብረት ያዘጋጀው የመጀመሪያው የዲጂታል ግብርና ጉባኤ በአዲስ አበባ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል። “ኢኖቬሽን እና የዲጂታል መፍትሄዎችን ለግብርና ዘርፍ በመጠቀም የአፍሪካን መጻኢ ጊዜ ብሩህ ማድረግ” የጉባኤው መሪ ሀሳብ ነው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊካ ሃዳዲ በጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር ኅብረቱ ዲጂታላይዜሽንን የልማት አጀንዳው አድርጎ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የግብርናው ዘርፍም በዚህ የዲጂታላይዜሽን አህጉራዊ ስትራቴጂ ውስጥ ትኩረት እንደተሰጠው አንስተዋል። ኮሚሽኑ አባል ሀገራት ለዲጂታል ግብርና የመረጃ አጠቃቀምና አስተዳደር አመቺ ፖሊሲዎችን እንዲያዘጋጁ እና እንዲተገብሩ ድጋፍ ያደርጋል ነው ያሉት። ለአርሶ አደሮች፣ ለግብርና ባለሙያዎችና ለወጣቶች በዲጂታል ክህሎቶች ዙሪያ ሥልጠና እንደሚሰጥም አረጋግጠዋል። በአፍሪካ ዲጂታል ግብርናን እውን ለማድረግ የአባል ሀገራት መንግስታት፣ የልማት አጋሮች፣ የግሉ ዘርፍ ተዋናዮች እና የምርምር ተቋማት በቅንጅት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል። የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ በበኩላቸው የአፍሪካን የግብርና ሥርዓት ለመለወጥ እና የምግብ ዋስትናን በዘላቂነት ለማረጋገጥ ዲጂታል ግብርናን መተግበር የግድ ነው ብለዋል። ዲጂታል ግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ የምርት ብክነትን ለመቀነስ፣ የፋይናንስና የገበያ ተደራሽነትን ለማስፋት እንዲሁም የመቋቋም አቅምን ለመገንባት ቁልፍ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ወጣቶች የአፍሪካ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ለኢኖቬሽንና ለዲጂታል ግብርና ትኩረት እንዲሰጡ ጠይቀዋል። ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ ትራንስፎርሜሽን ለማምጣት ዲጂታል ግብርናን እንደ ቁልፍ ስልት መውሰዷንና ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ዘርፉን ለማዘመን የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ በመድረኩ የተገኙት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ኢፋ ሙለታ(ዶ/ር) ገልጸዋል። የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎትን በስማርት ስልኮች አማካይነት ተደራሽ ማድረግ፣ ትክክለኛ የግብርና መረጃዎችን በአንድ ቋት መያዝና ማዘመን ላይ እየተሰራ መሆኑንና የግብርና ግብዓትን ተደራሽ ማድረግ፣ ከማሳ እስከ ገበያ ባለው ሂደት ውስጥ ያሉ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት ለማጎልበት ዲጂታላይዜሽን ላይ መሰራቱንም ጠቅሰዋል። የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ፣ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴሽን አገልግሎት፣ የግብርና ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን፣ የገበያ ተደራሽነት፣ የእሴት ሰንሰለትን ማጠናከር፣ የግብርና ምርታማነትን ከአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም መገንባት ጋር ያስተሳሰረ አካሄድን መከተል፣ የግብርና ፖሊሲዎችና የህግ ማዕቀፎች ትግበራ የኮንፍረንሱ ተሳታፊዎች የሚመክሩባቸው አጀንዳዎች ናቸው። ኮንፍረንሱ የእውቀት ሽግግር እና ፖሊሲ ተኮር ውይይቶች የሚደረግበት ሲሆን ስኬታማ የሀገራት የግብርና ኢኒሼቲቮች ለተሳታፊዎች ይቀርቡበታል። በአፍሪካ የዲጂታል ግብርና መፍትሄዎችን ተደራሽነት የሚደግፉ ስትራቴጂዎች የመለየት እና አጋርነቶችን ማጠናከር ከሁነቱ የሚጠበቅ አበይት ውጤት መሆኑን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የኢንተርኔት ተደራሽነት በሚፈለገው መጠን አለማደግ ፣ የዲጂታል ክህሎት ማነስ፣ የመሰረ ልማት ግንባታ እና የፖሊሲ ማዕቀፍ የዘርፉ ፈተናዎች ሲሆኑ ለአፍሪካ የዲጂታል ግብርና ትሩፋቶች ከፈተናዎቹ ይገዝፋሉ። ዲጂታል ግብርና ለአፍሪካ ዘላቂ ልማት፣ የምግብ ዋስትና መረጋገጥ እና ኢኮኖመሚ ልማት አንቀሳቃሽ ሞተር የመሆን አቅም አለው።
በቅሎ ወለደች
Nov 28, 2025 1235
ቦንጋ፤ሕዳር 19/2017(ኢዜአ)፦ዛሬ ከወደ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ያልተለመደ ክስተት ታይቷል። ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም እንዲሉ ጉዳዩ እንዲህ ነው፤ በክልሉ ዳውሮ ዞን ዛባ ጋዞ ወረዳ ያማላ ቦካ ቀበሌ አንዲት በቅሎ ወልዳለች። መውለድ ከማይችሉ እንስሳት ተርታ የምትመደበው በቅሎ የመውለዷ ነገር አዲስ ክስተት ሆኗል። ጉዳዩን በተመለከተ ኢዜአ ያነጋገራቸው የበቅሎዋ ባለቤት የሆኑት አቶ ነጋሽ በተላ በተፈጠረው ነገር እጅጉን መደናገጣቸውን ገልጸዋል። በቅሎ በተፈጥሮ እንደማትወልድ የሚታወቅ ቢሆንም በቤታቸው የተከሰተውን ነገር ማመን እንደከበዳቸው ነው የተናገሩት። ከወትሮ የተለየ ነገር እንዳላሳየችና ትላንትና ማታ ባልጠበቁት ሁኔታ ወልዳ መመልከታቸውን አቶ ነጋኝ አውስተው፤ በቅሎዋ ከወለደች በኋላ ምንም አዲስ ነገር እንዳላሳየችም አስረድተዋል። በዛባ ገዞ ወረዳ የማላ ቦካ ቀበሌ የእንስሳት ባለሙያው አቶ ደረጀ ደስታ ፤ ክስተቱ ከሳይንስና ከተፈጥሮም የሚቃረን ለማመን የሚከብድ መሆኑን ገልጸዋል። የተወለደው ፍጡር የፈረስ ቅርፅ ያለው ፣ ገና ፀጉር ያላበቀለና ቀኑ ያልደረሰ እንደሆነም አስረድተዋል። ሲወለድም የሞተ ሲሆን በቅሎዋ አሁን ላይ በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሆነችና ምንም የተለየ ምልክት እንዳላሳየችም ነው ለኢዜአ የገለጹት። ይህን አዲስ ክስተት ከተመለከቱ የአካባቢው ነዋሪዎች መካከል የአቶ ነጋኝ ጎረቤት የሆኑት አቶ ባሳ ፈልታሞ፥ይህ ነገር ለማመን የሚከብድ ክስተት ነው፤ ከዚህ በፊት እንዲህ ዓይነት ነገር ሰምቼም ሆነ አይቼም አላውቅም ሲሉ ገልጸዋል።
ድንበር ተሻጋሪው የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር ወዳጅነት
Nov 27, 2025 375
ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1969 ነው። ሀገራቱ በተለያዩ ክፍለ አህጉራት የሚገኙ ቢሆንም ርቀት ሳይገድባቸው በዲፕሎሲ እና ኢኮኖሚ መስኮች ያላቸውን ትብብር ቀጥለዋል። ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር በተለያዩ መስኮች ያላቸውን ግንኙነት ለማስፋት እየሰሩም ይገኛሉ። ሲንጋፖር በፍጥነት እያደገ የመጣውን የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ፣ ስትራቴጂካዊ ስፍራና ከፍተኛ የህዝብ ብዛት በመጠቀም ትስስሯን የማጎልበት ጠንካራ ፍላጎት አሳይታለች። እ.አ.አ በ2017 የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን እና የሲንጋፖር የሕብረት ስራ ኢንተርፕራይዝ የተፈራረሙት የጋራ መግባቢያ ስምምነት የዚሁ ማሳያ ነው። ስምምነቱ ሲንጋፖር በኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማትና የንግድ ስራ ምቹነት ሪፎርሞች ልምዷን የምታካፍልበት ነው። ሎጅስቲክስ፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ግብርና ማቀነባበሪያ፣ ማዕድንና ቱሪዝም ትብብራቸውን ለማጠናከር የጋራ ስምምነት ላይ ከደረሱባቸው መስኮች መከላከል ይጠቀሳሉ። ኢትዮጵያ ለሲንጋፖር የአፍሪካ የኢንቨስትመንት መግቢያ በር፣ ሲንጋፖር ለኢትዮጵያ የእስያ መግቢያ በር ናቸው ማለት ይቻላል። ሁለቱ ሀገራት በተደጋጋሚ የንግድ እና ኢንቨስትመንትን ጨምሮ አጠቃላይ ትብብራቸውን ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል። ሌላኛው የሀገራቱ የትብብር መስክ አቪዬሽን ነው። የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር አየር መንገዶች እ.አ.አ በ2012 የአየር አገልግሎት ትብብር ስምምነት መፈራረማቸው ይታወቃል። ስምምነቱ የመንገደኞችና ካርጎ በረራዎችን እንዲሁም የትራንስፖርት ትስስርን ለማጠናከር የሚያስችል ነው። የአየር አገልግሎት ስምምነቱ በምስራቅ አፍሪካና በደቡብ ምስራቅ እስያ መካከል በጉዞ፣ በካርጎ ንግድ እና ሎጅስቲክስ ያለውን ትብብር ለማጎልበት ያስችላል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እ.አ.አ በ2024 በሲንጋፖር ይፋዊ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወሳል። ጉብኝቱ ሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩበት 55ኛ ዓመት ክብረ በዓል ጋር የተገጣጠመ ነበር። በጉብኝቱ ወቅት ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር የጋራ መግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱ ሀገራቱ በመደበኛነት የሁለትዮሽ ምክክር እንዲያደርጉ፣ በትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ዘርፍ ያላቸውን ትብብር ማጠናከር የሚያስችል ነው። ሲንጋፖር በኢትዮጵያ ኤምባሲ እንደምትከፍት ይፋ አድርጋለች። የሲንጋፖር ውሳኔ ከኢትዮጵያ አልፎም ከቀጣናው ጋር በትብብር ለመስራት ያላትን የረጅም ጊዜ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ሆኗል። የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ዎንግ በቅርቡ በአዲስ አበባ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ከኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጋር በሁለትዮሽ እና በባለብዙ ወገን ትብብራቸው ዙሪያ መክረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ውይይቱ በሁለቱ ሀገሮች መካከል ያለውን ግንኙነት ለጋራ ነጋችን ወሳኝ በሆኑ መስኮች በጋራ ለመሥራት በምናደርገው ጥረት ውስጥ አንድ ጠቃሚ ርምጃ ነው ሲሉም ገልጸውታል። በተለይም በክሂሎት ልማት እና የካርበን ብድር ትብብር ላይ የተፈረሙት የመግባቢያ ስምምነቶች ጽኑ እና ለነገው ገበያ ዝግጁ የሆኑ ሠራተኞችን ለማፍራት ብሎም በአየር ንብረት ጥበቃ ረገድ ዘላቂ፣ ዝቅተኛ ካርበን የሚያወጣ እድገት ለማረጋገጥ ያለንን የጋራ አቋም ያንጸባርቃል ነው ያሉት። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም በላቀ ተግባራዊ ትብብር ንግድ እና ኢንቨስትመንትን በማስፋፋት፣ ዘመናዊ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስን በማልማት፣ በዲጂታል መሠረተ ልማት፣ በገንዘብ ልውውጥ ቴክኖሎጂ፣ ሳይበር ደኅንነትና ሰው ሰራሽ አስተውሎት ያለንን ትብብር ለመጠቀም እጅግ ሰፊ አቅም አለ ነው ያሉት። ሁለቱም መሪዎች በጉብኝቱ የኢኮኖሚ ትብብርን ለማላቅ፣ ተቋማዊ መስተጋብርን ለማጠናክር ብሎም የወል ቅድሚያዎቻቸውን ከፍ አድርጎ ለመከወን መንገዶችን እንደተመለከቱበትም ተናግረዋል። ሲንጋፖር በኢትዮጵያ ኤምባሲ ለመክፈት መወሰኗ ከኢትዮጵያ ባለፈ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ትስስር ማጎልበት የሚያስችላትን ማዕቀፍ እንደሚፈጥር የገለጹት ደግሞ የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ዎንግ ናቸው። ከዚህ በፊት የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር ኢትዮጵያን የጎበኙት እ.አ.አ በ1964 እንደነበር አስታውሰው የሁለቱን ሀገራት ትብብር ማጠናከር እና ለሲንጋፖር አዳዲስ የንግድ በሮች መክፈት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውን አመልክተዋል። አስተዳደር፣ ትምህርት እና ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ሀገራቱ ግንኙነታቸውን ለማጠናከር ከሚፈልጉባቸው መስኮች መካከል እንደሚጠቀሱ አንስተው የሀገራቱ መሪዎቹ በተገኙበት ከቁልፍ የጋራ ፍላጎቶቻችን ጋር የሚጣጣሙ የክህሎቶች ልማትና የካርቦን ገበያ የጋራ መግባቢያ ስምምነቶችን ተፈራረመናል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሲንጋፖር በአዲስ አበባ ኤምባሲ ለመክፈት መወሰኗን በደስታ እንደተቀበሉት ተናግረዋል። የኤምባሲው መከፈት ሲንጋፖር ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ብቻ ሳይሆን ከአፍሪካ ህብረት እና ከመላው አፍሪካ ጋር ቁልፍ ትስስር መፍጠሪያ ሆኖ እንደሚያገለግልም አመልክተዋል። ሲንጋፖር እና ኢትዮጵያ የየቀጣናቸው መግቢያ በር ናቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገራቱ ያላቸውን አጋርነት የበለጠ በማጠናከር ዜጎችን በዘላቂነት ተጠቃሚ የሚያደርግ ድልድል በደቡብ ምስራቅ እስያ እና አፍሪካ መካከል እየገነቡ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር የቅርብ ጊዜ ውይይቶችና የጉብኝት ልውውጦች ሀገራቱ በጋራ ለመልማትና ለማደግ ያላቸውን ቁርጠኝነት ያሳያል። የሁለቱ ሀገራት ትብብር በአፍሪካ እና በደቡብ ምስራቅ እስያ መካከል እንደ ድልድይ ሆኖ የሚያገለግል ነው።
በጥምር ግብርና ስኬት ያስመዘገቡት አርሶ አደር ወልዴ አርጋኒ
Nov 14, 2025 782
(በእንዳልካቸው ደሳለኝ - ከወልቂጤ ኢዜአ ቅርንጫፍ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጉራጌ ዞን ምሁር አክሊል ወረዳ ጨዛ ቀበሌ ነዋሪ ናቸው። ለዘመናት ባከናወኑት የግብርና ልማት ሥራ ኑሯቸው ከእጅ ወደ አፍ የዘለለ አልነበረም። ዛሬ ላይ ሆነው ያን ዘመንና ያሳለፉትን ዕድሜ ሲያስታውሱ ይቆጫሉ። በኋላ ቀር መንገድ ሲያከናውኑት ከነበረው የግብርና ልማት ሥራቸው ተጠቃሚ መሆንም፤ ሀብት ማፍራትም ሳይችሉ ቀርተዋል። አርሶ አደር ወልዴ አርጋኒ ይባላሉ። ከሰበሰቡት ሰብል ጎተራቸው ሳይጎድል፣ ከእንስሳት እርባታ ስራቸውም ጥገታቸው ሳትነጥፍ ማየት የዘውትር ህልማቸው ነበር። ለም መሬት ይዘው ምርታማ ባለመሆናቸው ሲቸገሩ፣ የሚሰራ ጉልበት ይዘው ማዕዳቸው እየጎደለ የጎልማሳነት ዕድሜ መባቻ ድረስ ችግር ሲፈራረቅባቸው ዓመታትን አሳልፈዋል። ይህ ፍላጎታቸው ሰምሮ፣ ጓሯቸው ለምቶ፣ ቤታቸው ሞልቶና ጥሪት አፍርተው የማየት ውጥናቸው ሳይሳካ ዓመታት ቢቆጠሩም ዛሬ ግን በጀመሩት የጥምር ግብርና ሥራ ነገሮች ተቀይረዋል። የዓመታት ምኞታቸውን ማሳካት ጀምረዋል። ከስድስት ዓመታት በፊት በትንሽ መሬት ላይ የጀመሩት የጥምር ግብርና ሥራ ለስኬት እንዲበቁ ከማድረግ ባለፈ በአካባቢያቸው አርአያ የሆኑ አርሶ አደር አድርጓቸዋል። የጥምር ግብርና ስራቸው ለዓመታት ከነበሩበት ከእጅ ወደ አፍ ኑሮ በማውጣት ለአፍም ለኪስም ሆኗቸዋል። የመንግስት የልማት ትኩረት የሆነው ጥምር ግብርና በውስን መሬት ላይ የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በቅንጅት እንዲያለሙ እድል ፍጥሮላቸዋል። በዋናነት በሰብል፣ በእንሰት፣ በፍራፍሬና በእንስሳት እርባታ ላይ አተኩረው እየሰሩ ይገኛሉ። ይህም የአንዱ ክፍተት በሌላው እየተሞለ ውጤታማ ስላደረጋቸው የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ ነው። ለቤት ፍጆታ ብቻ ያመርቱ የነበረው የእንሰት ምርትን በማስፋፋት ችግኙንና ተረፈ ምርቱን በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ጭምር ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ሆነዋል። የግብርና ግብዓቶችንና ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ተጠቅመው በሚያመርቱት ገብስ ለሌሎች አርሶ አደሮች ምሳሌ መሆን ችለዋል። ዝርያቸው የተሻሻሉ ላሞችን ስለሚያረቡም ወተት ከማጀታቸው አይጠፋም። በጓሯቸው የሚያለሙትን አትክልትና ፍራፍሬ ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ ማቅረብ የሚያስችል አቅም ፈጥረዋል። አርሶ አደሩ ከንብ ማነብ ሥራቸውም እንዲሁ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ነው። ከአካባቢው ስነምህዳር ምክንያት ብዙም ያልተለመደውን ቡና በመትከል ለፍሬ አብቅተዋል። የእሳቸውን ፈለግ የተከተሉ ሌሎች አርሶ አደሮችም ቡና ማልማት ጀምረዋል። በእጅ ያለን ሀብት ወደ ውጤት ለመቀየር ተግቶ መስራትና ጽናት ያስፈለጋል ያሉት አርሶ አደር ወልዴ፣ በግብርና ባለሙያዎች የተደረገላቸው ሙያዊ ድጋፍና የተፈጠረላቸው የገበያ ትስስር ለውጤታቸው ሚና እንዳለው ገልጸዋል። የእርሻ ልማትና የእንስሳት እርባታውን በቅንጅት ማከናወናቸውም እንዲሁ። አርሶ አደር ወልዴ የዓመታት ቁጭታቸው ዛሬ መፍትሄ እያገኘ ነው። የጥምር ግብርና ሥራቸው በምግብ ራሳቸውን እንዲችሉና ልጆቻቸውን በጥሩ ሁኔታ እንዲያሳድጉ አስችሏቸዋል። መኖሪያ ቤትን ጨምሮ የተለያየ ሀብት ለማፍራት ምክንያት በመሆኑም ልማቱን አስፋፍቶ ለማከናወን አቅደዋል። አርሶ አደር ወልዴ አርጋኒ ለአካባቢው አርሶ አደሮች ጭምር አርአያ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የጉመር ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሙራዱ ብሩ ናቸው። ቀደም ሲል በገብስ ምርት ላይ ብቻ አተኩረው ይሰሩ የነበረውን የግብርና ሥራ እንዲቀይሩ ምክንያት እንደሆኗቸው ይገልጻሉ። ከአርሶ አደር ወልዴ በወሰዱት ልምድ ወደ ጥምር ግብርና ገብተዋል። በዚህም ድርቅ የመቋቋም አቅም ያለውን እንሰት በማሳቸው በስፋት ማልማት ጀምረዋል። የነበሯቸውን ሀገረሰብ የዳልጋ ከብቶች በተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎች በመቀየር የተሻለ ተጠቃሚ ለመሆን ተግተው እየሰሩ ነው። ጥምር ግብርና የተሻለ ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ከአርሶ አደር ወልዴ ተምሪያለሁ ይላሉ። ከኢኮኖሚ ጠቀሜታው ባለፈ የመሬት ለምነትን ለማስጠበቅም ጠቀሜታው የጎላ በመሆኑ የጀመርነውን ሥራ እናጠናክራለን ሲሉም ነው የገለጹት። የሙህር አክሊል ወረዳ ግብርና ፅህፈት ቤት ሀላፊ መኑር ጀማል በበኩላቸው "አርሶ አደር ወልዴ አርጋኒ በውስን መሬት ገብስ፣ እንሰት፣ ቡና እና የተለያዩ ፍራፍሬዎችን በጥምር በማልማት የራሳቸውን ህይወት ከመቀየር ባለፈ ለሌሎች አርሶ አደሮች አርአያ እየሆኑን ነው ብለዋል። አርሶ አደሩ በሽታ መቋቋም የሚችሉና ለመድሃኒትነት የሚፈለጉ የእንሰት ዝርያዎችን በማፍላት ለገበያ እያቀረቡ ይገኛሉ። ከዚህም ባለፈ በመጥፋት ላይ የነበሩ የእንሰት ዝርያዎችን የመታደግና የአፈር ለምነት እንዲጠበቅ ጉልህ ሚና ማበርከታቸውንም ተናግረዋል፡፡ የጥምር ግብርና አሰራር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ስነ-ምህዳራዊ ጥቅሞችን የሚያስገኝ በመሆኑ በወረዳው ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ መሆኑን ነው የገለጹት። የአርሶ አደር ወልዴ ልምድን በማስፋት የሌሎች አርሶ አደሮችም ጓዳ ሞልቶ እንዲትረፈረፍ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው በተለይ በጥምር ግብርና አርሶ አደሩ ከራሱ ባለፈ ለሌሎች ጭምር እንዲተርፍ የማድርጉ ሥራ ይጠናከራል ብለዋል። ልማቱ እርስ በእርስ የሚደጋገፉና በአንድ መሬት ላይ የተለያዩ ምርቶችን በማግኘት የተሻለ ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው። ግብርናን ለማዘመንና ምርታማነትን ለማሳደግ በሚሰራው ሥራ ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች ውስጥ በጥቂት መሬት ብዙ ማምረት መቻል ነው። በመሆኑም በተለይ የመሬት እጥረት ባለባቸው አካባቢዎች ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ጠቀሜታው የጎላ ነው። በሥራ ውጤታማ ለመሆን ሁሉም ነገር ምቹና አልጋ በአልጋ መሆን የግድ እንዳልሆነ አርሶ አደሩ ጥሩ ማሳያ ናቸው። ወጣቶች በአካባቢያቸው ያለውን ዕድል እንዴት ወደሀብትነት መቀየር እችላለሁ ብለው ከሰሩ ውጤታማ እንደሚሆኑ የእሳቸው የስኬት ጉዞ በቂ ማሳያ ነው። ሰርቶ ለመለወጥም ሆነ ሀብት ለማፍራት ችግሮችን በጽናት ማለፍ እና የሥራ ትጋት ወሳኝ ነውና ተሞክሯቸውን ማስፋት ያስፈልጋል።
"ከትውስታ ወደ አዲስ ተስፋ"
Nov 12, 2025 720
"ከትውስታ ወደ አዲስ ተስፋ" ብርሃኑ ፍቃዱ -ከሰቆጣ የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ መልካዓምድራዊና ኢኮኖሚያዊ መሰረት ያለው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒሰትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቅርቡ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ ላይ ማብራራታቸው ይታወሳል። ኢትዮጵያ የባህር በሯን ያጣችበትን የ30 ዓመታት ታሪክ ለመቀልበስ ይህን ያህል ዓመት እንደማይወስድ አጽንኦት ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ የባሕር በር ያጣችበት መንገድ ሕጋዊና ተቋማዊ መሰረት የሌለው የሚያስቆጭ ብሔራዊ ጥቅም ስብራት አካል ስለመሆኑም አንስተዋል። አቶ መለሰ ይሄይስ እና አቶ አድማሱ ደሳለኝ፤ የኢትዮጵያ የባሕር በር የተወለዱበት ስፍራ፣ የኖሩበት ቀዬ፣ ያሳደጋቸው ማህበረሰብ ... የዘመናት ትዝታና ትውስታቸው እንደሆነ ይገልጻሉ። ይህን የታሪካቸው አካል የሆነውን የባሕር በር ማጣትም የሁል ጊዜ ፀፀትና እንደ ሰውነት ጥላ አብሮዋቸው የሚዞር እውነታ ነው። ከአካባቢው ርቆ ለሚገኝ ሰው ትውስታውን ሲያወራ ለሌላው ተረት ተረት፤ ለራስ ደግሞ የውስጥ ቁስል ማገርሸት ሆኖ ነው የሚሰማው ይላሉ። ኢትዮጵያም የአሰብ ወደብንና የቀይ ባህር መዳረሻን በፖለቲካዊ ሸፍጥ ማጣቷ በቀይ ባህር ላይ እየዋኙ፣ ውሃ እየተራጩ፣ በዳርቻው ነፋሻማ ስፍራ እየተዝናኑ... ለኖሩት ለእነ መለሰ እና አድማሱ መቼም የማይረሳ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የባሕር በር ጉዳይ ለኢትዮጵያ የህልውና ጉዳይ መሆኑን ለአለም ማሕበረሰብ ጥያቄውን ሲያሳውቁ ተደብቆ ለቆየው ትውስታቸው አዲስ ተስፋ እንደሰጣቸውም ለኢዜአ ተናግረዋል። አቶ መለሰ ይሄይስ በአሰብ የነዳጅ ማጣሪያ ማዕከል ለ12 ዓመታት እንዳገለገሉ በትውስታና ቁጭታቸውን ወደ ኋላ ተመልሰው ያወሳሉ። አሁን በሰቆጣ ከተማ የሚኖሩት አቶ መለሰ ይሄይስ ፤ የአሰብ ወደብ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ በማፋጠን የበኩሉን አስተዋጽኦ በማበርከት ተደማሪ አቅም ነበር በወቅቱ ይላሉ። ይህን የአሰብ ወደብንና የቀይ ባሕር መዳረሻን በፖለቲካዊ ሴራ ኢትዮጵያ ስታጣ ይሰሩበት ከነበረው የአሰብ የነዳጅ ማጣሪያ ስራ አቁመው ወደ ትውልድ ስፍራቸው ሰቆጣ መምጣታቸውን አውስተዋል። በራሳቸው ላይ ከደረሰባቸው የስራ እና ሃብትና ንብረት ማጣት ፣ እንግልትና ሌሎች ችግሮች በላይ ኢትዮጵያ ከባሕር በር የተነጠለችበትን ሁኔታ ሲያስቡና ሲያሰላስሉ እንደሚያስቆጫቸው ይገልጻሉ። ኢትዮጵያ የቀይ ባሕርን በማጣት የባሕር በር ብቻ ሳይሆን የገቢና ወጭ ንግድን፣ የነዳጅ ማጣሪያ ጭምር ነው ያጣችው ያሉት አቶ መለሰ፤ አሁን ጥያቄው መነሳቱ ኢትዮጵያን ወደ ቀደመ ገናናነቷ ለመመለስ ያለመ አበረታች ተግባር እንደሆነ ተናግረዋል። መንግስት ያነሳው የባሕር በር ጥያቄም የዘመናት ቁጭታችንን፣ ብስጭታችንን እና ህልማችንን ከተደበቀ ትውስታ፤ ወደ አዲስ ተስፋ የወሰደ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ ህጋዊና ታሪካዊ ነው ያሉት አቶ መለሰ ፤ ጥያቄው በሰላማዊ መንገድ እልባት እንዲያገኝም ለአዲሱ ትውልድ በማስተማርና ግንዛቤ በመፍጠር የበኩላቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል። ከ1973 ዓ.ም ጀምረው ለአስር ተከታታይ ዓመታት በአሰብ ወደብ የሲቪል መሃንዲስ ክፍል ሰራተኛ እንደነበሩ ያወሱት አቶ አድማሱ ደሳለኝ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የባሕር ባር ባለቤት በሆነችባቸው ዘመናት ገናና እና የተከበረች ሀገር ሆና መቆየቷን አንስተዋል። የባሕር በሩ የኢትዮጵያ የገቢና ወጭ ንግድ የሚሳለጥበት እንደነበር አስታውሰው፤ ይሄን ታላቅ ትሩፋትና ፀጋ ለማስመለስ የተጀመረው እንቅስቃሴ ቁጭትና ትውስታችንን ወደ አዲስ ተስፋ የቀየረ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በታሪካዊ ጠላቶችና ባንዳዎች እኩይ ሴራ የባሕር በር ካጣች ወዲህ ጥያቄውን ማንሳት የማይቻልበት የአፈናው ዘመን አክትሞ በለውጡ መንግስት መነሳቱ አበረታችና ለማስመለስም ከፍተኛ መነቃቃት የፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። እኔም ባለኝ አቅም ሁሉ ስለባሕር ባር አስፈላጊነት፣ ጥቅምና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ግንዛቤ በመፍጠር ለስኬታማነቱ የድርሻዬ እወጣለሁ ሲሉም ገልጸዋል።
ባሕር በር -የታሪክና የእድገት ስብራት ወጌሻ
Nov 5, 2025 769
ባሕር በር የታሪክ እና የእድገት ስብራት ወጌሻ በቀደሰ ተክሌ የምሥራቅ አፍሪካዋ ታላቅ ሀገር ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ስሟ ገኖ እንዲነሳ ካደረጓት መካከል የሰው ዘር መገኛነት፣ የራሷ የሆነ የአስተዳደር ሥርዓት፣ የዘመን አቆጣጠር፣ ቋንቋና ፊደል ያላት ሉዓላዊት ሀገር መሆኗ ተጠቃሽ ነው ። የገናና የጥበብ ባለቤት መሆኗን አክሱም እና ላሊበላ ዛሬም ቆመው ይመሰክሩላታል። በጥንት ጊዜ ወደብ የስልጣኔ ተጽዕኖ ፈጣሪነት መገለጫ በነበረበት ጊዜ ኢትዮጵያም ስሟ ጎልቶ ይነሳ ነበር። ወደብ ዓለምን እርስ በእርስ ከማስተሳሰር ባለፈ የግብይት የጀርባ አጥንት ሆኖ ሲያገለግል ቆይቷል፤ ዛሬም እያገለገለ ይገኛል። ሀገራት አዋጭ የንግድ ስትራቴጂ ቀይሰው የተለያዩ ወደቦችን የመጠቀም ልምዳቸው በታሪክ ውስጥ ጎልቶ የሚነሳ ነው። የንግድ ሥርዓታቸውን በወደብና በየብስ ከሚያከናውኑ የዓለም ሀገራት መካከል ደግሞ ኢትዮጵያ አንዷ ናት። የታሪክ ድርሳናት እንደሚያሳዩት ኢትዮጵያ በተለያዩ ዘመነ መንግስታት የተለያዩ ወደቦችን በባለቤትነት አስተዳድራለች። ከአክሱም ዘመነ መንግሥት ጀምሮ እስከ ደርግ መንግስት ድረስ አዱሊስ፣ አሰብ፣ ዘይላ፣ ምጽዋና ሌሎች ወደቦችን ለኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች ትገለገል ነበር። ይሕ የኢትዮጵያ የወደብ ባለቤትነት ታሪክ እስከ 1983 ዓ.ም ድረስ የዘለቀ እንደነበር በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሰቲ የታሪክ እና ቅርስ አስተዳደር ትምሕርት ክፍል መምሕር አጥናፉ ምትኩ ይናገራሉ። ወደብ ከኢኮኖሚያዊ ጥቅም ባሻገር ፖለቲካዊ እና ማኅበራዊ ፋይዳው ከፍተኛ እንደሆነም አውስተዋል። በታሪክ ኩነት ውስጥ የተፈጠረ ሴራና ተንኮል ኢትዮጵያ የባሕር በር አልባ ሀገር እንድትሆን አድርጓታል። ይሕም ከሆነ ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ ተቆጥሯል። በዚሕም ኢትዮጵያ ለወደብ ኪራይ በየዓመቱ ብዙ ቢሊዮን ብር እየከፈለች የወጪ እና ገቢ ንግድን የማንቀሳቀስ እዳ ተጭኖባታል። ይሕም የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ወደ ኋላ ከሚጎትቱ ጉዳዮች አንዱ ሆኖ ዛሬ ድረስ ዘልቋል። የወደብ አገልግሎት ነጻነት ማጣት፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶች ዋጋ መጨመር፣ ማዳበሪያን ጨምሮ አስፈላጊ ግብአቶች መዘግየትና በወቅቱ አለመድረስ፣ በዚሕም የሰብል ልማት ስራዎች ላይ ችግሮች መስተዋል ከባሕር በር ባለቤትነት እጦት ጋር የመያያዝ እድላቸው ሰፊ ነው። እነዚሕ ችግሮች ደግሞ ተደማምረው ለኑሮ ውድነት መፈጠር አስተዋጾኦ ይኖራቸዋል ማለት ይቻላል። በታሪክ አጋጣሚ የተፈጠረው ስብራት እያስከተለ ያለው ጉዳት አሁን ላይ ለኢትዮጵያ የሕልውና ጉዳይ በመሆኑ በታሪካዊ ዳራ መሠረት መጠገን ያስፈልጋል። ለኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ከ130 ሚሊዮን ያሻቀበ የሕዝብ ቁጥር፣ የኢኮኖሚ ዕድገትና ሀገራዊ የቆዳ ስፋት ገፊ ምክንያቶች ከሚባሉት ውስጥ ይጠቀሳሉ። በሌላ በኩል ከዚሕ ቀደም የነበረው የሀገሪቱ ባሕር በር ባለቤትነት ማስረጃ ዛሬ ላይ አስቻይ ሁኔታን የሚፈጥር ነው። መንግሥት የጀመረው የባሕር በር ባለቤት የመሆን ጥያቄ በመሬት ተዘግቶ የመኖር ታሪክ እንዲያበቃ የሚያደርግና በዓለም አቀፍ ሕግ ተፈጥሮን በጋራ ተጠቅሞ የመልማት መብትን የሚያስጠብቅ መሆኑ እውን ነው። ለሦስት አስርት ዓመታት ታፍኖ የቆየው የቀይ ባሕር ባለቤትነት ጥያቄ የመንግስት ቁርጠኝነት እንዳለ ሆኖ ዜጎችም አጥብቀው በመያዝ መልስ እስኪያገኝ ድረስ መስራት ይጠበቃል። የሀገርና የሕዝብ የዘመናት ጥያቄ የሆነው የባሕር በር እስኪሳካ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ሥራ መሥራት ከሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደሚጠበቅ መምሕር አጥናፉ ይገልጻሉ። ለኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤት መሆን የታሪኳና ዕድገቷ ወጌሻ ነው ያሉት መምሕር አጥናፉ ኢትዮጵያ የባሕር በር ለመጠቀም የሚያስችላት ታሪካዊ መብት አላት። ይሕን ታሪካዊ መብቷን የምታረጋግጥበት ትልቁ መሣሪያ ደግሞ ያላት ጠንካራ የዲፕሎማቲክ አቅሟ ነው። ከዓለም ሀገራት ጋር ያላት መልካም ግንኙነት ተናግሮ ለማሳመን እውነታን ለመግለጽ የሚያስችላት ነው። ይሕንንም በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በዓለም ፊት አረጋግጣለች። ይሕን የሕዳሴ ድል በቀይ ባሕር ላይ የማትደግምበት ምንም ምክንያት አይኖርም። በተለይ ኢትዮጵያ ያላት የጋራ ተጠቃሚነት መርሕ በዓለም ላይ ተቀባይነት ያለውን ሀሳብ ይዛ እንድትቀርብ እያስቻላት ይገኛል። ለጎረቤት ሀገራት ቅድሚያ የሚሰጠው የውጭ ግንኙነት ፖሊሲዋ ተፈጥሮን ተባብሮ በማልማት እንጠቀም የሚል መሠረት ያለው ነው። መምሕር ይስሐቅ ንጉሤ በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሰቲ የምጣኔ ሀብት መምሕር ሲሆኑ የባሕር በር ጉዳይ የኢኮኖሚ ዕድገት ማጠንጠኛ ሆኖ የሚያገለግል መሆኑን አንስተው ኢትዮጵያ የባሕር በር ማጣቷ በፈጣን ዕድገቷ ላይ መሰናክል ሆኖ መዝለቁን ተናግረዋል። በተለይ የዓለም ሀገራት ከፍተኛው የንግድ፣ የኢኮኖሚና ሀብት እንቅስቃሴ የሚታይበት እና የሀገራት የንግድ ልውውጥ የሚካሄድበት የቀይ ባሕር ቀጠና ላይ ያለውን አብሮ የመስራትና ከማደግ ዕድል ኢትዮጵያ ያለአግባብ መገለሏን ያነሳሉ።ይሕም በሀገሪቱ ምጣኔ ሀብታዊ ዕድገትና በሌሎች ላይ ያሳደረው አሉታዊ ተጽዕኖ ከፍተኛ እንደሆነ ነው ያገለጹት። የባሕር በር ጥያቄ የምጣኔ ሀብት ዕድገትን በማሳለጥ ሀገሪቱ ከልመና ለመውጣት ያላትን ዕድል እንድትወስን ያስችላታል የሚሉት መምሕሩ ፤ለስኬቱም የተጀመረውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ማጠናከር እንደሚገባም ነው የገለጹት። እንደ መምሕሩ ገለጻ ከዓለም አቀፍ መርሆችና ስምምነቶች እንዲሁም ካለን መልከአ ምድራዊ አቀማመጥና ታሪክ አንጻር ለኢትዮጵያ የባሕር በር ተገቢ ነው። ይሕ እንዲሳካም መንግስት ካሳየው ቁርጠኝነት በተጨማሪ ሁሉም በተቀናጀ መንገድ የሚያደርገውን ጥረት ማጠናከር ይኖርበታል። መንግስት የዘመናት የትውልዱ ጥያቄ ሆኖ የቆየውን የባሕር በር ጉዳይ በግልጽና በይፋ መረጃ በመስጠት ዓለም አቀፍ አጀንዳ እንዲሆንም ጭምር እያደረገ ያለውን ጥረትንም አድንቀዋል። ታሪክ በኩነቶች መካከል መጥፎም መልካም ሆኖ ያልፋል። በታሪክ የባሕር በር ባለቤትነታችን የገጠመውን ስብራት ለመጠገን የሚያስችል ወጌሻ ያስፈልጋል። በታሪክ ሂደት መልካሙ ወደ መጥፎ ሁኔታ እንደሚቀየር ሁሉ የተበላሸን ወደ መልካም የመቀየር ዕጣ ፈንታ ያለው የዛሬው ትውልድ ላይ ነው። ለእዚሕ ደግሞ ትውልዱ በሕዳሴው ግድብ ከመንግስት ጎን ሆኖ ያሳየውን አንድነትና ሕብረት በባሕር በርም መድገም አለበት። ታሪካዊ ዳራን፣ ዲፕሎማሲን፣ ሀገራዊ ነባራዊ ሁኔታና ሕግን ተከትሎ በአብሮነት ከተሰራ ያኔ የተበላሸው ይቃናል፤ ያጣነውን እናገኛለን። "እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል" ዓይነት እንስሳዊ ግብር በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሊሰማ አይገባም፤ መሰማትም አይኖርበትም። ኢትዮጵያ ብታደግ ለቀጣናው ኩራት፤ ለአፍሪካም ልዕልና እንጂ ጥፋት የሚያስከትል እንዳልሆነ መገንዘብና የትብብር ልማትና ዕድገትን ባሕል ማድረግ ሊለመድ ይገባል። ሰላም!
የዳሰነቾች ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴ ''ጀለባ''
Oct 30, 2025 1313
የዳሰነች ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴ ''ጀለባ'' (በጣፋጩ ሰለሞን ከጂንካ ኢዜአ ቅርንጫፍ) ዳሰነቾች በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በደቡብ ኦሞ ዞን ውስጥ ከሚገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ጋር በአብሮነት ተጎዳኝተው ይኖራሉ። የብሔረሰቡ አባላት ዋነኛ መተዳደሪያ ከብት እርባታ ሲሆን፤ ከከብት እርባታው ጐን ለጐን በዝቅተኛ ደረጃ በግብርናና በዓሳ ማስገር ስራ ይተዳደራሉ፡፡ ዳሰነቾች በሰሜን ከሐመር፣ በደቡብ ከኬኒያ፣ በምስራቅ ከቦረና በስተ ምዕራብ ደግሞ ከኛንጋቶም ማህበረሰብ ተጎራብተው ይኖራሉ። ዳሰነቾች ከኩሽቲክ የቋንቋ ነገድ የሚመዘዝ ''አፍ ዳሰነች'' የተሰኘ የመግባቢያ ቋንቋም አላቸው። ዳሰነቾች የተለየ የአለባበስ፣ የአጋጌጥ፣ የቤት አሰራር እና የባህላዊ የሙዚቃ ስልተ ምትን ጨምሮ አስደማሚ ባህሎች እና ማራኪ የመልክዓ ምድር አቀማመጥን የታደሉ ናቸው። ዳሰነቾች ከሚታወቁባቸው አስደማሚ ባህሎች ውስጥ አንዱ የሆነው አለመግባባቶችን በውይይት የሚፈቱበት የ''ጀለባ''ስርዓት ተጠቃሽ ነው። ይህ ስርዓት ግጭቱ ቂምና ቁርሾ በማይሻገርበት መልኩ በዘላቂነት የማስወገድ አቅም ያለው ሲሆን የማይናወጥ ሰላምና ወንድማዊ ትስስር እንዲጠናከርም ሚናው የጎላ ነው። ዕሴቱ የዳሰነቾች የአኗኗር ቁመና የሚለካበትና የሚመዘንበት መጻኢንም የሚተለምበትም ጭምር ነው። ስለሆነም በዳሰነቾች ዘንድ ቂም መያዝ አሎሎ ተሸክሞ እንደመዞር ይቆጠራል ነው የሚባለው። የባህሉ ተመራማሪ ሊዮን አርሎት 'ጀለባ'' የተሰኘው ባህላዊ ዳኝነት ከአካባቢው ሰላም አልፎ ለቀጠናው ወንድማማችነት መጠናከር ትልቅ ሚና ያለው የፍትህ ስርዓት መሆኑን ያነሳሉ። በ''በጀለባ'' ስርዓት ባህላዊ የዳኝነት አሰጣጥ እርከኖች እንዳሉ ጠቅሰው፥ አለመግባባቶች ሲፈጠሩ ''ኖሞ'' የተሰኙ ሽማግሌዎች ወደ ስፍራው በማቅናት የግጭቱን መንስኤ በማጣራት ''ቶሎል'' ለተሰኙ ሌሎች ሽማግሌዎች የሚያሳውቁበት አሰራርም አላቸው። እንደ ግጭቱ ቅለትና ክብደት ''ቶሎል'' በተሰኙ ሽማግሌዎች ተለይቶ ቀለል ያለው ''ካባና'' በተሰኙ ዳኞች ውሳኔ የሚሰጥ ሲሆን፥ ጉዳዩ ከበድ ያለ ከሆነ ደግሞ የመጨረሻው ውሳኔ ''አራ'' በተሰኙ ዳኞች ይሰጣል። ከነፍስ ማጥፋት በስተቀር ሁሉም ውሳኔዎች ''አራ'' በተሰኙ ዳኞች እልባት ያገኛሉ። የነፍስ ማጥፋት ወንጀል ሲከሰት ግን ጉዳዩን ለመንግሥት አሳልፎ በመስጠት ጉዳዩ በፍርድ ቤት ውሳኔ እንዲያገኝ ይደረጋል ። ነፍስ ያጠፋው ሰው የእርምት ጊዜውን አጠናቆ ማህበረሰቡን ለመቀላቀል ሲወስን ባህላዊ የዕርቅ ስነ-ስርዓት ተዘጋጅቶ በዳይና ተበዳይ ይቅር የሚባባሉበትም ስርዓት እንዳለ የባህሉ ተመራማሪ ይናገራሉ። በዳሰነቾች ባህል ልዩነቶች ሰላማዊ በሆነ መንገድ በዘላቂነት መንገድ የመፍታት ዘመናትን የተሻገረ ድንቅ ዕሴት መኖሩን የሚያነሱት የብሔረሰቡ አባል አሸቴ ነካሲያ፤ “በዳሰነች ብሔረሰብ ቂም መያዝ አሎሎ ተሸክሞ እንደመዞር ይቆጠራል'' ይላሉ። በዳሰነቾች አለመግባባቶች በውይይት የሚፈቱበት ስርዓት እንዳለ ጠቅሰው፥ ''ናብ'' በተሰኘው የዳኝነት ስፍራ አለመግባባቶች ውለው ሳያድሩ እልባት ያገኛሉ ብለዋል። ሌላው የብሔረሰቡ አባል ሎቶያቡስ ሎኪሰሬሬ በበኩላቸው የባህል መሪዎች የተጣላን ማስታረቅ፣ ትውልዱን የመግራትና በስነ-ምግባር የማነፅ ኃላፊነት እንዳላቸው ጠቅሰዋል። ''ማንም ሰው ከባህል መሪዎች ትዕዛዝ አያፈነግጥም'' የሚሉት አቶ ሎቶያቡስ፥ ሁሉም እርስ በእርስ በመከባበር እና ችግሮች ሲኖሩ በውይይት በመፍታት አብሮነቱን ያጠናክራል ብለዋል። ወጣቱ ለባህል መሪዎች ታዛዥ ነው የሚሉት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ የብሔረሰቡ አባል ሎሲያ ሎብቻ ወጣቶች ለአካባቢው ሰላም ዘብ እንዲቆሙ፣ ከአጎራባች ህዝቦች ጋር በፍቅር እንዲኖሩ በማስተማር ወጣቱን በስነ-ምግባር የማነፅ ስራ እንደሚሰሩም ተናግረዋል። የዳሰነች ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታደለ ሀቴ በበኩላቸው የዳሰነች ህዝብ ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴ ከወረዳው አልፎ ለቀጠናው ሰላም ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክቷል ብለዋል። የብሔረሰቡ ባህላዊ የሽምግልና ስርዓት ትውልዱን በመግራት በስነ- ምግባር የታነፀ ዜጋ እንዲፈጠር እንዳደረገም አስረድተዋል። የጂንካ ዩኒቨርሲቲ የሶሻል አንትሮፖሎጂ መምህርና ተመራማሪ አጎናፍር ሰለሞን፤ ባህላዊ የዳኝነት ስርዓቶች ለዘመናዊው የፍትህ ስርዓት መጠናከር ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ብለዋል። ባህላዊ የግጭት አፈታት ሥርዓቶች ቅጣት በመጣል ጥፋተኝነት እንዲሰማ የሚያደርጉ ሳይሆኑ፤ እውነተኛ ይቅርታን የሚያሰፍኑና ለአብሮነት የሚበጁ ዕንቁ ባህሎች እንደሆኑም አብራርተዋል። ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎቹ በግለሰብ ተጠቃሚነት ላይ ሳይሆን በማህበረሰብ ተጠቃሚነት ላይ ትኩረት የሚያደርጉ በመሆናቸው ከዘመናዊው የፍትህ ስርዓት በይበልጥ ለአብሮነት መጠናከር አስተዋጽኦ እንዳላቸውም ገልጸዋል። ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎቹም ለሀገራዊ መግባባት ሚናቸው የላቀ በመሆኑ፥ እሴቶቹ ተጠብቀው፣ ለምተውና ጎልብተው ጥቅም ላይ እንዲውሉ መስራት እንደሚገባም መክረዋል። ሀገራችን ቂምና ቁርሾን የወለዱ ያለመግባባቶች በዘላቂነት በሰለጠነና ሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በማቋቋም ሁሉንም ያሳተፈ ስራ እየሰራች እንደሆነ ያነሱት መምህርና ተመራማሪው አጎናፍር ሰለሞን ዕሴቶቹ በማህበረሰቡ ዘንድ ካላቸው ተቀባይነት እንዲሁም ሀገራዊ የምክክር ሂደቱን ከማገዝ አንጻር ጉልህ ሚና ስለሚኖራቸው መጠቀም እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
''ቦር ተራራ'' የየሞች የፈውስ ምድር
Oct 27, 2025 733
(በእንዳልካቸው ደሳለኝ ከወልቂጤ ኢዜአ ቅርንጫፍ) የም ዞን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውስጥ ይገኛል። በዞኑ የቦር ተራራ ዋነኛው የመድኃኒት እጽዋት መገኛ እና ምንጭ በመሆኑ የሞች በየዓመቱ ጥቅምት ወርን ጠብቀው በ17ኛው ቀን ከዚህ ተራራ በህብር ሆነው የመድኃኒት እጽዋት ለቀማ ስነ-ስርዓት ያካሂዳሉ፤ ይሰባስባሉም ። የቀደምት የየም አባቶችና እናቶችን በማሳተፍ የሚከወነው የመድኃኒት እጽዋት ለቀማ ከባህር ጠለል በላይ 2 ሺህ 939 ሜትር ከፍታ ላይ በሚገኘው ቦር ተራራ ላይ ነው። በዚህ ተራራ ላይ በየዓመቱ ጥቅምት 17 ቀን የሞች ለዓመት የሚያገለግላቸውን የመድኃኒት እጽዋት ይለቅማሉ። ተግባሩንም አዋቂዎች በጋራ ሰብሰብ ብለው ለመድኃኒት የሚውለውን ቅጠል በጥሰው፣ ስር ምሰው፣ አስሰውና መርጠው ይሰበስባሉ። ይህም የመድኃኒት እጽዋት ለቀማ ስርዓት "ሳሞ ኤታ" ተብሎ ይጠራል ። አያምጣውና ህመም ሲከሰት ታማሚውን ሰው ወይም እንስሳን ከበሽታው ለመፈወስ የተዘጋጀው ባህላዊ መድሃኒት በባህላዊ ሃኪም ትዕዛዝ መሰረት በህመሙ ልክ ይታዘዝለታል። መድሃኒቱን ለመጠቀምም የጠቢባን አባቶችን ፈለግ ተከትሎ መፈፀም የግድ ይላል። የሞች አጅግ አስገራሚ እና አስደናቂ የሆኑ የበርካታ አገር በቀል ዕውቀቶች ባለቤት ናቸው ካስባሏቸው እሴቶች መካከል ይህ ለየት ያለው ክዋኔያቸው አንዱ ነው፡፡ አባቶች ታዳጊና ወጣቶችን አስከትለው ወደ ቦር ተራራ በመውጣት የሚፈፅሙት ባህላዊ ክዋኔ በመሆኑም ከትውልድ ወደ ትውልድ ቅብብሎሹን ጠብቆ እስከ አሁን እንዲዘልቅ እድርገውታል። በየሞች ዘንድ የባህላዊ መድኃኒት አዋቂዎች ከሚባሉት መካከል አንዱ አቶ ጌታቸው ሃይለማርያም፤ የመድኃኒት ዕፅዋት ለቀማ ልምድን የቀሰሙት ከአባታቸው መሆኑን በመግለፅ አያታቸው ከቅድመ አያቶቻቸው በመውረስ እዚህ እንዳደረሱት ይናገራሉ። የቦር ተራራ ለመድሃኒት ዕፅዋት ለቀማው የተመረጠበትን ምክንያት ሲያስረዱም ቦታው ተራራ በመሆኑ ማንም ያልደረሰባቸው የተለያዩ እፅዋትን ለማግኘት አመቺ ከመሆኑ ጋር ያያይዙታል። በሌላም በኩል ጠዋት ፀሐይ ስትወጣ መጀመሪያ የምታገኘው ተራራውን በመሆኑና ክረምቱ አልፎ ጥቅምት ሲገባ የተለያዩ ቅጠላ ቅጠሎችን በብዛት እና በዓይነት ለማግኘት ተመራጭ ወቅት መሆኑም ቦታው የተመረጠበት ሌላኛው ምክንያት ነው ብለዋል። በጥቅምት 17 ለመድኃኒትነት የሚያገለግለው ዕፅዋት ቅጠልም በየፈርጁ ተለቅሞ እና ተቀምሞ ይቀመጣል ሲሉም አስረድተዋል። የተዘጋጀው ባህላዊ መድኃኒትም ለሰው ልጆችና ለቤት እንስሳት ያገለግላል ሲሉም አስረድተዋል፡፡ ይኸው በዚህ ቀን የተለቀመው የመድኃኒት ዕፅዋት ከዚህኛው ጥቅምት 17 እስከሚቀጥለው ዓመት ጥቅምት 17 ድረስ እንደሚያገለግልም አቶ ጌታቸው አስረድተዋል፡፡ የባህል መድኃኒት ሰብሳቢዎች እና ተጠቃሚዎች ጊዜውን ጠብቀው ከተለያዩ ቦታዎች ወደ ቦር ተራራ እንደሚመጡ የሚገልጹት የባህል መድኃኒት አዋቂው ዛሬ ዛሬ እሳቸውን ጨምሮ መድኃኒት ቤቶችን በመክፈት ፈዋሽነታቸው የተረጋገጡ የባህል መድኃኒቶችን በመሸጥ ኑሯቸውን እየመሩ የሚገኙ አያሌ የአካባቢው ነዋሪዎች እንዳሉም ይናገራሉ። ሌላኛው የባህል መድኃኒት አዋቂው አቶ ወልደመስቀል ጆርጋ በበኩላቸው በየሞች ዘንድ የተዘጋጀው የመድኃኒት ዕፅዋት ጥቅም ላይ የሚውለው ህመም ሲያጋጥም ብቻ ሳይሆን በሽታን አስቀድሞ ለመከላከል መሆኑን ጠቁመው መድኃኒቶቹም ብቻቸውን እንዲሁም ከምግብ ጋር በመመገብ ለጥቅም እንደሚውሉም አንስተዋል። የየም ምድር የበርካታ የመድኃኒት ዕፅዋቶች መገኛ አካባቢ " የፈውስ ምድር " ነው የሚሉት ደግሞ በየም ባህላዊ መድኃኒት ዙሪያ ጥናት ያደረጉት በጅማ ዩኒቨርሲቲ የፎክሎር መምህር እና ተመራማሪ ለማ ንጋቱ (ዶ/ር) ናቸው። ከየሞች አያሌ የባህል ዕሴቶች መካከል የባህል መድኃኒት ለቀማና ቅመማ አንዱና ዋነኛው የሀገር በቀል እውቀት ማሳያ መሆኑን ገልፀው የመድኃኒት ዕፅዋት ለቀማ ስነ-ስርዓቱ ከጥንት ጀምሮ ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተሸጋገረ ዛሬ ላይ የደረሰ እንደሆነም ያስረዳሉ፡፡ ማህበረሰቡ የራሱንም ሆነ የእንስሳትን ጤና የመጠበቅ የቆየ ባህል ያለው መሆኑን በጥናት መረጋገጡን ጠቅሰው የባህላዊ መድኃኒት ለቀማው ከሊቅ እስከ ደቂቅ የሚሳተፉበት ዓመታዊ ክዋኔ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ ሌላው ገራሚው ነገር ይላሉ አጥኚው ታላላቆች ታናናሾቻቸውን አስከትለው የለቀማ ሂደቱን የሚያስረዱበት መንገድ ደግሞ ስርዓቱ ለመጪው ትውልድ እንዲተላለፍ የሚያስችል ትውልድ ተሻጋሪ የሀገር በቀል እውቀት ሽግግር ስርዓት ማሳያ እንደሆነም ነው የገለጹት። በዚህም ሂደት የሚነገሩ ስነ-ቃሎች መሞጋገስ፣ ጭፈራና ደስታ ይስተናገድባቸዋል። ይህም ማህበራዊ ትስስርን ይበልጥ የሚጠናክሩበትን ሁነት የሚፈጥር ስርዓት ነው። የየም ዞን ባህል እና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ አቶ መስፍን ሞጋ በበኩላቸው የቦር ተራራ የመጀመሪያውን የማለዳ የፀሐይ ጎህ የሚፈነጥቅበት የንጋት ብርሃን ቀድሞ የሚያገኝ በመሆኑ፥ በዚህ አካባቢ የሚገኙ እጽዋት በሽታን የመከላከልና ፈዋሽነታቸው ከፍተኛ ነው ተብሎ ስለሚታመን ለዚህ ክዋኔ ቦታው መመረጡን ነው የሚገልፁት። ለዚህም ነው የሞች ይህንን ስፍራ ከሌሎች ቦታዎች አስበልጠው የሚወዱት፤ በየዓመቱም ጥቅምት 17 ቀን ወደ እዚህ ስፍራ በማቅናት ለዓመት ፍጆታ የሚያገለግላቸውን መድኃኒትም ይሰበስቡበታል ብለዋል። ጥቅምት 17 በየም ዘንድ ለየት የሚያደርገው ሌላው የመድሃኒት ዕፅዋት ለመልቀም እና ለመጠቀም ብቻ ሳይሆን የለቀማውን ትዕይንት ለመመልከት የሚመጡ ቱሪስቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመሩ መምጣታቸው ሌላው ትልቁ ትሩፋት ነው ይላሉ። የመድኃኒት ዕፅዋት ለቀማው ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የሚሳተፉበት በመሆኑ፥ ለአብሮነት እና ሃገር በቀል እውቀት ለመቅሰም ከፍተኛ ሚና እንዳለውም ነው አቶ መስፍን የገለፁት።
የአፍሪካ የግብርና፣ ውሃ እና ከባቢ አየር አጀንዳ፤ እድሎች እና ፈተናዎች
Oct 20, 2025 838
አፍሪካ ዘላቂ ልማትን ለማሳካትና እንድትበለጽግ የጀመረችው ጉዞ ወሳኝ መዕራፍ ላይ ይገኛል። የአህጉሪቱን የመለወጥ ትልም ባሏት እምቅ ተፈጥሯዊ ጸጋዎች ላይ የተመረኮዘ ነው። ተዝቆ የማያልቀው የአፍሪካ ብዝሃ ሀብት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግና አይበገሬ አቅም መገባንት የሚያስችሏትም ጭምር ናቸው። ግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የውሃ ሀብቶቿ እና ብዝሃ ከባቢ የአየር ንብረቷ ከሀብቶቿ መካከል ይጠቀሳሉ። ግብርና አሁንም የአፍሪካ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ነው። ዘርፉ ለአህጉሪቱ 35 በመቶ የሚጠጋ አጠቃላይ ጥቅል ሀገራዊ ምርት(ጂዲፒ) አስተዋጽኦ ያደርጋል። 60 በመቶ ህዝብም በግብርና ስራ እንደሚተዳደር የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የልማት ፕሮግራም (ካዳፕ) ሰነድ ያሳያል። ከዚህም ውስጥ አብዛኞቹ አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮች ናቸው። ሴቶች በግብርናው ዘርፍ ካለው የሰው ኃይል የ50 በመቶ ድርሻው ይወስዳሉ። የአፍሪካ ህዝብ 60 በመቶ ድርሻ የያዘው ወጣት በግብርና ንግድ፣ እሴት መጨመርና የኢኖቬሽን ስራዎች ያለው ተሳትፎ እያደገ መጥቷል። የዓለም 60 በመቶ ያልለማ መሬት ያለው በአፍሪካ ነው። ሰፊ የውሃ ሀብቶችና እያደገ ያመጣው ብሉ ኢኮኖሚ(የባህር እና ሌሎች የውሃ ሀብቶች) ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ እድገትን የሚያረጋግጡ ናቸው። የመሰረተ ልማቶች ተደራሽነት ማደግ፣ ቀጣናዊ የእሴት ሰንሰለቶችና ኢኖቬሽንን የተመረኮዙ የፋይናንስ አማራጮችን መስፋት ግብርናን የምግብ ምንጭ ብቻ ሳይሆን ለኢንዱስትሪ ልማት፣ የስራ ዕድል ፈጠራ እና ንግድ መሳለጥ ትልቅ አቅም መሆን ይችላል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና በግብርና ምርቶችና አገልግሎቶች ያለውን አህጉራዊ የእርስ በእርስ የንግድ ልውውጥ በማሳደግ ረገድ ትልቅ ዕድል ይዞ የመጣ ነው። የንግድ ቀጣናውን በሚገባ መጠቀም ከተቻለ እ.አ.አ በ2030 የግብርና ንግድ ልውውጡን በ30 በመቶ ማሳደግ እንደሚቻል ጥናቶች ያመለክታሉ። ግብርናው የተጠቀሱት ጥንካሬዎች ያሉት ቢሆንም ረጅም ጊዜ የዘለቁ መዋቅራዊ ፈተናዎች አብረውት ዘልቀዋል። የግብርና ምርቶች ላይ የሚፈለገውን ያህል እሴት አለመጨመር፣ የቴክኖሎጂ አጠቀቃምና የምርታማነት ውስንነት፣ የመሰረተ ልማቶች እና ሎጅስቲክስ በበቂ ሁኔታ አለመሟላት፣ ተቋማዊና አስተዳደራዊ ክፍተቶች ከአየር ንብረት ለውጥና ሌሎች ተፈጥሯዊ አደጋዎች እንዲሁም እያደገ ከመጣው ህዝብ ጋር ተዳምሮ ግብርናውን እየፈተነው ይገኛል። ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት የአፍሪካ የግብርና ትራንስፎርሜሽን አጀንዳ ማጠንጠኛ የሆነው ጉዳይ የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት(ካዳፕ) ነው። እ.አ.አ በ2003 የአፍሪካ ህብረት በሞዛምቢክ ባደረገው ስብሰባ የግብርና የምግብ ዋስትና ድንጋጌን አጽድቋል። ይህ ማዕቀፍ የማፑቶ ድንጋጌ ስያሜን በማግኘት የካዳፕ ትግበራ በይፋ እንዲጀመር አድርጓል። የማፑቶ ድንጋጌ እ.አ.አ በ2014 በማላቦ ድንጋጌ (ከእ.አ.አ 2014 እስከ 2025 የተተገበረ) በአዲስ መልክ የታደሰ ሲሆን የተለያዩ ቃል ኪዳኖችን በውስጡ ይዟል። ይህም በካዳፕ አማካኝነት የአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት ከአጠቃላይ ዓመታዊ ጥቅል ምርታቸው(ጂዲፒ) ቢያንስ ስድስት በመቶውን ለግብርናው ዘርፍ እንደሚመድቡና በየሀገራቱ በዘርፉ በየዓመቱ በአማካይ ስድስት በመቶ እድገትን የማሳካት ግብ አለው። ረሃብን ማጥፋት፣ ድህነትን በግማሽ መቀነስ፣ የማይበገር አቅም መገንባትና የጋራ ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ሌሎች ግቦች ናቸው። ካዳፕ የአፍሪካ ሀገራት በስርዓተ ምግብ ያላቸውን ኢንቨስተመንት በማሳደግ፣ በአፍሪካ የእርስ በእርስ የግብርና ንግድን በማሳደግና የፖሊሲ መሰናሰልን በመፍጠር ቁልፍ ሚና ተወጥቷል። ይሁንና የተመዘገቡት ውጤቶች ያልተመጣጠነ ልዩነት የሚታይባቸው ናቸው። የ2023 የካዳፕ የግምገማ ሪፖርት እንደሚያሳየው የአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት የማላቦ ግቦችን ማሳደግ የሚያስችል መንገድ ላይ እንዳልሆኑ ያስቀምጣል። ይሁንና 26 ሀገራት በተቀመጡ ግቦች መመዘኛ መሻሻል እንዳሳዩ ይገልጻል። ኢትዮጵያ፣ ብሩንዲ፣ ካሜሮን፣ ግብጽ፣ ማሊ፣ ጋና እና ጋምቢያ የተሻለ አፈጻጸም ካላቸው ሀገራት መካከል ይጠቀሳሉ። አብዛኞቹ ሀገራት በግብርና ኢንቨስትመንት፣ ምርታማነት እና የፖሊሲ ትግበራ ላይ ፈተናዎች እንዳሉበት ሪፖርቱ አመልክቷል። ሀገራት የሰነዱን ትግበራ ማፋጠንና ተቋማዊ ቅንጅትን ማጠናከር እንደሚገባቸው አሳስቧል። የማላቦ ድንጋጌ ወደ መገባደዱ ላይ የሚገኝ ሲሆን የካዳፕ ቀጣዩ ምዕራፍ የካምፓላ ድንጋጌ ነው። ይህ የትግበራ ምዕራፍ ከእ.አ.አ 2026 እስከ 2035 የሚቆይ ነው። የካምፓላ ድንጋጌ ከማፑቶ እና ማላቦ ድንጋጌዎች ትምህርቶችን በመውሰድ የግብናውን እድገት ማላቅ ግቡ አድርጎ ይዟል። የካምፓላ አጀንዳ ኢኖቬሽን፣ ዲጂታላይዜሽን፣ አረንጓዴ እድገት እና አይበገሬነት ያላቸውን ሚና በማንሳት መስኮቹ ስርዓተ ምግብን ዘላቂና አካታች የማድረግ ግብን ማሳካት እንደሚያስችሉ አመልክቷል። በዚህ ማዕቀፍ እ.አ.አ 2050 2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ህዝብ ይኖራታል ተብሎ የሚጠበቀውን አፍሪካን በራስ አቅም የመመገብ ውጥን የያዘ ነው። ይሁንና የግብርና ምርታማነት ከዓለም አቀፍ አማካይ የምርታማነት ምጣኔ አንጻር ሲታይ አሁንም ወደ ኋላ ቀረት ያለ ነው። ይህም አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮች የተገደበ የፋይናንስ አቅርቦት ማግኘታቸው እንዲሁም የቴክኖሎጂ ተጠቃሚነትና የገበያ ትስስር እንዲፈጠርላቸው አለመደረጉ የችግሩ አብይ መንስኤ ሆኖ ይጠቀሳል። የአየር ንብረት ለውጥ ፈተናዎችና የከባቢ አየር ብክለት ፈተናዎቹ እንዲበረቱ አድርጓል። ዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ የበይነ መንግስታት ፓናል(IPCC) አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ማጣጣሚያ እርምጃዎችን በፍጥነት ካልወሰደች እ.አ.አ በ2050 የግብርና ምርታማነቷ ከ20 እስከ 30 በመቶ ሊቀንስ እንደሚችል ገምቷል። ከ250 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ አፍሪካውያን ደህንነቱ ያልተረጋገጠ እና ንጽህናው ያልተጠበቀ የውሃ አቅርቦት ፈተና ውስጥ ይገኛሉ። በህዝብ ቁጥር መጨመር፣ በከተሜነትና ኢንዱስትሪ መስፋፋት ምክንያት ንጹህ የውሃ አቅርቦትን የማግኘት ጉዳይ የበለጠ ሊስፋ እንደሚችል ተመላክቷል። የአፍሪካ ህብረት የተቀመጡ ግቦች እንዲሳኩና ፈተናዎች ዘላቂ መፍትሄ እንዲያገኙ ለአባል ሀገራት የፋይናንስ እና የቴክኒክ ድጋፎችን እያደረገ ይገኛል። የህብረቱ የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ ከባቢ አየር የስራ ክፍሉ(DARBE) አማካኝነት የአፍሪካን ፖሊሲዎች፣ ፕሮግራሞችና ኢኒሼቲቮች የተናበቡና የጋራ ግብ ያላቸው እንዲሆኑ ክትትልና ድጋፍ ያደርጋል። የአቅም ግንባታ፣ የቴክኒክ እና የፖሊሲ ድጋፍም የሚያደርግ ሲሆን ብሄራዊ እቅዶች ከአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ሰነዶችና የአጋርነት ማዕቀፎች ጋር የተጣጠሙ መሆናቸውን ያረጋገጣል። የስራ ክፍሉ ከቀጣናዊ የኢኮኖሚ ማህበረሰቦች፣ የግሉ ዘርፍና የልማት አጋሮች ጋር አጋርነቶችን የማጠናከር ስራ ያከናውናል። ግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ አስተዳደር፣ የአየር ንብረት ለውጥ አይበገሬነት እንዲሁም የተፈጥሮ እና የብሉ ኢኮኖሚ ሀብቶች በዘላቂነት መጠቀም ላይ የተቀናጁ አሰራሮችን መፍጠር ላይም ይሰራል። የዘርፉ አጠቃላይ ስራዎች አካል የሆነው ስድስተኛው የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ጥቅምት 11 ቀን 2018 ዓ.ም በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ መካሄድ ይጀምራል። በስብሰባው ላይ ሚኒስትሮች፣ ባለሙያዎችና የልማት አጋሮች ይሳተፋሉ። የአፍሪካ የግብርና ኢኒሼቲቮች አፈጻጸም መገምገምና ዘርፉ ሁሉን አቀፍና ዘላቂ ማድረግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ መምከር የስብሰባው አላማ ነው። እ.አ.አ በ2023 በአዲስ አበባ የተካሄደውን አምስተኛው የልዩ ኮሚቴ ስብሰባ ውጤቶች ግምገማ ይደረጋል። የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት ፕሮግራም(ካዳፕ) የማላቦ ድንጋጌ(ከእ.አ.አ 2014 እስከ 2025) ስኬቶች እና የካዳፕ የካምፓላ ድንጋጌ (ከእ.አ.አ 2026 እስከ 2035) አፈጻጸም ላይ ውይይት ይካሄዳል። የስርዓተ ምግብን ማጠናከር፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ምርታማነት ስርዓት መዘርጋት፣ የበካይ ጋዞችን ልህቀት መቀነስና ዘላቂ የውሃና የተፈጥሮ ሀብቶች አስተዳደርን ማጠናከር ሌሎች የምክክር አጀንዳዎች ናቸው። በአፍሪካ በገጠር አካባቢ የሚኖሩ ዜጎችን ኑሮ በማሻሻል ዘላቂ እድገትን ማምጣት በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ምክረ ሀሳቦች ይቀርባሉ። ውይይቱ እ.አ.አ በ2026 በአዲስ አበባ የሚካሄዱትን የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባና የህብረቱ የመሪዎች ጉባኤ የሚሆኑ አጀንዳዎችን እንደሚያዘጋጅ ተመላክቷል። የአፍሪካ ህብረት ግብርና፣ የገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር አጀንዳ 2063 ለማሳካት ቁልፍ ሚና የሚጫወቱ ዘርፎች መሆናቸውን አመልክቷል። ህብረቱ የግብርና እና የገጠር ልማት የበለጠ ማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝም አመልክቷል። የህብረቱ አባል ሀገራት የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት ፕሮግራምን በተጠናከረ ሁኔታ እንዲተገብሩም ጥሪ አቅርቧል። ስድስተኛው የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ ጥቅምት 11 እና 12 እንዲሁም ጥቅምት 14 በሚኒስትሮች ደረጃ እንደሚያከናውን ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። አፍሪካ ወደ ዘላቂ ግብርና፣ የገጠር ልማት፣ ውሃ አስተዳደር እና አካባቢ ጥበቃ እያደረገች ያለው ጉዞ አንገብጋቢ አጀንዳና ሽግግሩን ለማፋጠን ወሳኝ ሚና አለው። አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የፋይናንስ ማነቆ፣ መሰረተ ልማቶች እና የፖሊሲ የመፈጸም አቅም ውስንነትን ጨምሮ የተለያዩ ፈተናዎች ቢኖሩባትም እድሎቿ ፈርጀ ብዙ ናቸው። በርካታ ያልለማ መሬት፣ ሰፊ የውሃ ሀብት፣ ወጣቶች እና የብሉ ኢኮኖሚ ሀብቶች በአፍሪካ ዘላቂ የግብርና እድገት ለማረጋገጥና ሁሉን አቀፍ ስርዓተ ምግብ ለመገንባት የሚያስችል ነው። ለአርሶ አደሮች በቂ የፋይናንስ አቅርቦት ተደራሽ ማድረግን ጨምሮ አቅማቸውን መገንባት ቁልፍ ጉዳይ ነው። ሀገራት ብሄራዊ ፖሊሲዎቻቸውን ከአህጉራዊ ማዕቀፎች ጋር ማጣጣም ይኖርባቸዋል። ግቦችን ለማሳካት የተቀናጀ የባለድርሻ አካላት የአሰራር ማዕቀፍ መዘርጋት ይገባል። የተፈጥሮ ሀብትን በሚገባ መጠቀም፣ በኢኖቬሽን ላይ መዋዕለ ንዋይን ፈሰስ ማድረግና አህጉራዊ ትብብርን ማጠናከር የምግብ ዋስትናዋን ያረጋገጠች፣ አረንጓዴ እና የበለጸገች አህጉር መገንባት ይቻላል።
ኢሬቻ ለሁለንተናዊ ሀገራዊ ማንሰራራት!
Oct 3, 2025 1359
ኢሬቻ የምስጋና በዓል ነው፤ ሰዎች በክረምት ወቅት ከሚከሰት መለያየትና መራራቅ በኋላ ዳግም የሚገናኙበት፣ በአብሮነት ብርሃን ለማየት ያበቃቸውን ፈጣሪ የሚያመሰግኑበት ዕለት ነው። ስለ ሰላምና አንድነት የሚዘመርበት፣ ስለመጪው ጊዜ መልካም ምኞት የሚገለጥበት፣ ሁሉን ላደረገ ፈጣሪ ምስጋና የሚቸርበት የአብሮነት በዓል ነው። ኢሬቻ የሰው ልጅ ከተፈጥሮ ጋር ያለው ጥብቅ ቁርኝት የሚገለጽበት የገዳ ስርዓት አንዱ አካል ነው፡፡ የኢሬቻ እሴቶች ጠንካራ ህብረ-ብሔራዊ አንድነት ያላት ሀገር ለመገንባት የሚያግዙ ናቸው። አንድነት፣ ወንድማማችነት፣ አብሮነት፣ ሰላም፣ ፍቅር፣ ዕርቅ እና ሌሎችም ተጠቃሽ የመልካም እሴቶች መገለጫ ነው። በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ ሳይንስ እና ባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በማይዳሰስ ቅርስነት የተመዘገበው የገዳ ስርዓት አንዱ እሴት ኢሬቻ ሲሆን፤ ለሀገር ማንሠራራትና ሁለንተናዊ ብልጽግና መረጋገጥ መሠረት ይሆናል፡፡ ኢሬቻ አብሮነት የሚጸናበት፣ የወንድማማችነትና እህትማማችነት እሴት ይበልጥ የሚጎላበት፣ አሰባሳቢ ትርክት የሚጎለብትበት፣ ሁሉም በጋራ የሚያከብረው የፍቅር፣ የአንድነት እና የአብሮነት ማሰሪያ ከፍ ያለ በዓል ነው፡፡ ኢሬቻ በጋራ የሚያከብሩትና የዓለም ቱሪስቶች የሚታደሙበት ሲሆን፤ ሕብረ ብሔራዊ አንድነትና የኢትዮጵያ ድንቅ ባህል ጎልቶ የሚታይበት ነው፡፡ የዘንድሮውን የኢሬቻ በዓል አከባበር ሀገራዊ ማንሰራራት በተግባር የተረጋገጠበት ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ተመርቆ ዓለም የኢትዮጵያን መቻል በተግባር ባየበትና ሌሎች ለሀገር ማንሰራራት ዕውን መሆን መሠረት የሚጥሉ ትላልቅ ሀገራዊ ኘሮጀክቶች ይፋ በተደረጉበት ማግስት መሆኑ ለየት ያደርገዋል፡፡ በዓሉ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የመላው ኢትዮጵያዊያንን ሕብረት የሚንጸባረቅበት ሆኖ በተለያዩ አከባቢዎች በድምቀት እየተከበረም ይገኛል፡፡ በልመናው፣ በምርቃቱ፣ በምስጋናው ሁሉ ሀዬ! ሀዬ! ሀዬ! (አሜን! አሜን! አሜን!) የሚሉ ድምፆች ይስተጋባሉ። Hayyee! Hayyee! Hayyee! Hayyee! Hayyee! Hayyee! Waaqa Uumaa, Waaqa Uumamaa ፍጥረትን የፈጠርክ ፈጣሪ Gurraacha garaa garbaa የእውነትና የሰላም አምላክ! Dogoggora nu oolchi ከስህተትና ከክፉ ነገሮች ሁሉ ጠብቀን! Dacheef nagaa kenni ለምድራችን ሰላም ስጥ! Laggeenif nagaa kenni ለወንዞቻችን ሰላም ስጥ! Olota keenyaaf nagaa kenni ከጎረቤቶቻችን ጋር ሰላም ስጠን! . . . Loowan keenyaaf nagaa kenni " ለሰውም ለእንስሳቱም ሰላም ስጥ!" በማለት ይመረቃል። ሕዝቡም ይሁንልን ይደረግልን ሲል "አሜን! አሜን! አሜን!” ይላል። የዘንድሮው የኢሬቻ በዓል መስከረም 24 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሆራ ፊንፊኔ እንዲሁም በማግስቱ እሑድ መስከረም 25 ቀን በቢሾፍቱ ሆራ ሀርሰዲ " ኢሬቻ ለሀገር ማንሰራራት " በሚል መሪ ሐሳብ ይከበራል። የክራምት ወራት እንዳበቃ የሚከበረው "ኢሬቻ መልካ" Irreecha Birraa (በውኃ ዳርቻ የሚከበር) ሲሆን፤ በዓመቱ አጋማሽ ላይ "ኢሬቻ ቱሉ" Irreecha Arfaasaa ደግሞ በተራራማ ቦታ ይከበራል። ኢሬቻ መልካ የሚከበረው በመስከረም ወር ከመስቀል በዓል በኋላ ነው። የክረምት ወራት የዝናብ፣ የደመና፣ የጭቃና የረግረግ ወቅት አልፎ ለፈካው ወራት በመምጣቱ ምስጋና የሚቀርብበት ነው። ይህ ከማህበራዊ መስተጋብር አኳያም ሰዎች የሚሰባሰቡበትና የሚገናኙበት ነው። ከባዱ የክረምት ወቅት አልፎ ብርሃን (ብራ) ስለደረሰ ለዚያ ምልክት ይሆን ዘንድ የለመለመ እርጥብ ሣር ይዘው ወደ ወንዝ በመውረድ ንጹህ ውሃ ውስጥ እየነከሩና እየረጩ ለፈጣሪ ምስጋና የሚያቀርቡበት ነው፡፡ ኢሬቻ ቱሉ የሚከበረው የበጋው ወራት አልፎ የበልግ ዝናብ በሚጠበቅበት ወቅት ነው። በዚህም ፈጣሪ ''እርጥበት አትንፈገን፣ ወቅቶች ጊዜያቸውን ጠብቀው ይምጡ፤ የዝናብ ንፋስ ስጠን'' በማለት ለፈጣሪ ተማጽኖ የሚቀርብበት ነው። "ይህን ተራራ የፈጠርክ ፈጣሪ ወቅቱን የሰላም አድርግልን፣ የሰላም ዝናብ አዝንብልን፣ ጎርፍን ያዝልን፣ የተዘራው ፍሬ እንዲያፈራ እንለምንሃለን" እያለ በኢሬቻ ቱሉ ላይ ፈጣሪውን ይለምናል፡፡ በኢሬቻ በዓል የፈጣሪ ምህረት፣ ዕርቅ፣ አብሮነት እና በዓሉ የሰላም በዓል እንዲሆን ከላይ በተጠቀሰው መልኩ ኦሮሞ ፈጣሪውን ይጠይቃል፤ ይማፀናል፤ ለተደረገለትም ነገር ሁሉ ያመሰግናል። ኢሬቻ ምድርን እና ሰማይን ለፈጠረው "ዋቃ" "Waaqa" ምስጋናውን ለማድረስ የሚከበር ሲሆን፤ በዕድሜ ልዩነት ሳይገደብ ለዘመናት በጋራ፣ በአንድነትና በፍቅር ሲከበር ቆይቷል። በዝናባማው የክረምት ወቅት በጅረቶችና ወንዞች መሙላት ምክንያት ተራርቆ የቆየው ዘመድ አዝማድ በኢሬቻ በዓል ማክበሪያ ሥፍራ ይገናኛል፤ ይጠያየቃል፤ ናፍቆቱንም ይወጣል። አባቶች ክረምት በለሊት ይመሰላል ይላሉ። ለሊት ደግሞ ጨለማ ነው። ጨለማው ሲነጋ ደግሞ ብርሃን ነው፤ ብርሃን ደግሞ ውበት ነው፤ መታያና መድመቂያም ነው። ለዚህ ነው በኢሬቻ በዓል አከባበር ላይ ሁሉም ውብ የባህል ልብሱን በመልበስ በደስታ በዓሉን ለማክበር የሚመጣው። ሕዝቡ በዓሉ ወደ ሚከበርበት ሥፍራ የሚሄደው በተናጠል ሳይሆን በሕብረትና በአንድነት ነው፡፡ ለዚህ ነው ኢሬቻ የአንድነትና የአብሮነት በዓል ነው የሚባለው። ኢሬቻ የወንድማማችነትና የአንድነት አርማ ሲሆን፤ የብሩህ ዘመን ማብሰሪያ፣ የህብረ ብሔራዊ አብሮነት ማስተሳሰሪያም ጭምር ነው፡፡ በኢሬቻ ልዩነት የለም፤ ፀብ የለም፤ ክፋት የለም፤ ይልቁንም ምስጋና ይበዛል፤ ፍቅር ይሰፍናል፤ አብሮነት ያብባል፣ አንድነት ይጸናል። ኢሬቻ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው የሰላምና የአብሮነት ምልክት ነው። የኢሬቻ በዓልን ለማክበር የሚወጣው ታዳሚም እንደ እርጥብ ሣር ወይም አበባ ያለ እርጥብ ነገር በእጁ ይዞ የበዓሉን ስነ-ስርዓት ያከናውናል። ይህን የሚያደርገውም "ፈጣሪያችን ሆይ አንተ ያፀደቅከው ነው አብቦ ፍሬ ያፈራው፤ ለዚህም እናመሰግንሃለን" በማለት የፈጣሪን መልካምነት ለማሳየት ነው። በሌላ በኩል እርጥብ ሣር የልምላሜ ምልክት በመሆኑ የመልካም ምኞት መግለጫም ስለሆነም ነው በኢሬቻ በዓል እርጥብ ሣር የሚያዘው። የኢሬቻ በዓል ሲከበር ከሚከወኑ ሥርዓቶች መካከል ሴቶች ሲቄ፣ እርጥብ ሣር እንዲሁም ጮጮ ይዘው ከፊት ሲመሩ አባ ገዳዎች ደግሞ ቦኩ፣ አለንጌ እና ሌሎችንም በበዓሉ ሥርዓት የሚፈቀዱትን ሁሉ በመያዝ ወደ ሥርዓቱ አከባበር እንዲህ እያሉ ያመራሉ። ኦ ያ መሬሆ…………………መሬሆ መሬሆ………………… መሬሆ ያ ዋቃ ኡማ ሁንዳ መሬሆ………………… ያ መሬሆ መሬሆ………………… መሬሆ ያ ዋቃ ለፋ ኡምቴ መሬሆ………………… ያ መሬሆ መሬሆ………………… መሬሆ ያ ዋቃ መልካ ኡምቴ መሬሆ………………… ያ መሬሆ መሬሆ………………… መሬሆ እያሉ ያመራሉ። የሁሉ ፈጣሪ፣ ምድርን የፈጠርክ፣ ወንዙን የፈጠርክ . . . ምስጋና ለአንተ ይሁን በማለት ያመሰግናሉ፤ ይዘምራሉ። የኢሬቻ በዓል ሥነ-ሥርዓት በአባመልካ ተከፍቶ በአባ ገዳዎች ተመርቆ ከተጀመረ በኋላ መላው ሕዝብ በአንድነት ሥርዓቱን ያከናውናል። ኢሬቻ ሁሉም በጋራ የሚያከብረው፣ የሁሉም ማጌጫ፣ መድመቂያ እና የአብሮነት መገለጫ ነው። የበዓሉ ታዳሚዎች ከዋዜማው ጀምሮ በሆረ ፊንፊኔና በሆረ ሀርሰዲ በመሰባሰብ፤ የተለያዩ ባህላዊ ጭፈራዎችን በማዜምና ምስጋና በማቅረብ አድረው በነጋታው ዋናውን የምስጋና በዓልም ያከናውናሉ፡፡ የበዓሉ ታዳሚዎች የደስታና የምስጋና ምልክት የሆነውን ባህላዊ ነጫጭ ልብስ ለብሰው፣ ባህልን የሚያንፀባርቁ የተለያዩ ሁነቶችን በመከወን ልዩ ልዩ ዜማዎችን በማዜም፣ ግጥሞችን በማቅረብ፣ ወደ ፈጣሪ በመጸለይ እና ምስጋና በማቅረብ ሥርዓቱን ያከናውናሉ፡፡ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች የሚታወቁበትን ባህላዊ ልብስ በመልበስ በቋንቋቸው ፈጣሪን እያመሰገኑ በዓሉን በአንድነት ያከብራሉ። ከሃገር ውስጥና ከውጭ ሀገር በርካታ ታዳሚዎች የሚሳተፉበት የኢሬቻ በዓል የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦችን ከማቀራረብና ህብረ ብሔራዊ አንድነትን ከመገንባት ረገድ ትልቅ አስተዋጾኦ ያለው ነው፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ-ኢትዮጵያውያን የሆራ ፊንፊኔ እና የሆራ ሀርሰዲ በዓላት ላይ ለመታደም ወደ አገር ቤት ይመጣሉ። የውጭ አገራት ጎብኚዎችና እንግዶችም በትዕይንቱ ይታደማሉ። ለአብነትም ባሳለፍነው ዓመት ከኬንያ፣ ሩዋንዳ እና ታንዛኒያ አገር የመጡ ልዑካን በበዓሉ ላይ በመታደም የበዓሉን ትልቅነት እና የኢትዮጵያውያን የአብሮነት መገለጫ መሆኑን መመስከራቸው ይታወሳል። አያሌ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳዎች ያሉት ይህ የምስጋና በዓል እውነተኛ ወንድማማችነት የሚታይበት፣ አንድነት የሚጎላበት፣ አብሮነት የሚጠናከርበት፣ ሰላምና ተስፋ የሚታወጅበት አገራዊ እሴት ነው። በባህል አልባሳትና ጌጣጌጦች፣ ባህላዊ ምግቦችና ሌሎች ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ግለሰቦችና ተቋማት ኢሬቻና መሰል የአደባባይ በዓላትን እንደመልካም የገበያ አማራጭ ይጠቀሙባቸዋል። የኢሬቻ በዓል ለቱሪዝም ፍሰት የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ጉልህ ነው፤ በርካታ የባህር ማዶ እና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎች የሚታደሙበት በዓል ነው፡፡ በዓሉ ትልቅ የቱሪዝም መስህብ ሲሆን፤ ዘርፉን በማጠናከር እና ብሔራዊ ልማትን በማሳደግ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ከፍ በማድረግ ረገድ ትልቅ ሚናንም የሚጫወት ነው፡፡ ኢሬቻ ባህላዊ አልባሳትና ቁሳቁሶች በስፋት የሚተዋወቁበት ታላቅ መድረክ ነው። በእርግጥም ይህንን ውብ የጋራ እሴት ጠብቆ ለትውልድ ማስተላለፍ ያስፈልጋል። ኢሬቻ የምስጋና በዓል ነውና በምስጋና እንደጀመርን በምስጋናና ምርቃት እንሰነባበት። "ሀዬ! ሀዬ! ሀዬ! ከመጥፎ ነገር ጠብቀን! ንጹህ ዝናብ አዝንብልን! ከእርግማን ሁሉ አርቀን! እውነትን ትቶ ከሚዋሽ አርቀን! ከረሃብ ሰውረን! ከበሽታ ሰውረን! ከጦርነት ሰውረን! ሀዬ! ሀዬ! ሀዬ!
በትግራይ ክልል የመስቀል በዓል አከባበር
Sep 27, 2025 1258
የመስቀል በዓል በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች በልዩ ድምቀት ከሚከበሩ በዓላት መካከል አንዱ ነው። በዓሉ እንደየአካባቢው ባህላዊና ሃይማኖታዊ ትውፊቱን ጠብቆ በተለያዩ ሁነቶች ይከበራል። በትግራይ ክልልም የመስቀል በዓል እንደሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች ሁሉ በናፍቆት ከሚጠበቁና በድምቀት ከሚከበሩ በዓላት ተርታ ይመደባል። ለዚህም ሲባል የተለያዩ ዝግጅቶች ከበዓሉ ዋዜማ በፊት እንዲጠናቀቁ የሚደረግ ሲሆን፥ በተለይ በየዓመቱ መስከረም 16 እና 17 ዘመድ አዝማድ ተጠራርተው የሚገናኙበት የፍቅርና የአብሮነት በዓል ሆኖ ይከበራል። የክርስቶስ ግማደ መስቀል በንግስት ኢሌኒ አማካኝነት መገኘቱን በማሰብ በየዓመቱ መስከረም አጋማሽ ላይ የሚከበረው የመስቀል በዓል የመስቀል ኃያልነት፣ እውነት በተደበቀበት ለዘላለም እንደማይቀርና ፍቅርን አብዝቶ የሚሰበክበት ከዚህ ባለፈም እርቅ የሚወርድበትና ደስታ የሚገለጽበት አጋጣሚ መሆኑም ይገለጻል። በትግራይ የበዓሉን ታላቅነትና ክብር ለማድመቅ ምእመናን ጽዱ ልብስ ለብሰውና የተለያዩ ዝማሬዎችን በማሰማት ደመራ ወደሚደመርበት ሥፍራ ችቦ ይዘው በመሄድ ደምራውን በማቀጣጠል የሚያከበሩት ሲሆን፣ በእለቱ የቤት እንስሳት ጭምር ቀንዳቸውና ጀርባቸው ላይ ቅቤ ተቀብተው እንዲያርፉ ይደረጋል። ዘመድ አዝማድ፣ ጎረቤታሞች፣ አብሮ አደጎችና የበዓሉ ታዳሚ እንግዶችም ተሰባስበው ማለዳ ላይ ገንፎ በማዘጋጀት ይመገባሉ። የእንስሳት እርድ በማከናወን ባህላዊ መጠጦችን በማዘጋጀት በዓሉን የፍቅር፣ የመሰባሰብ፣ የአንድነትና ተካፍሎ የመብላት በዓል መሆኑን በተግባር የሚያሳይበት ክስተት ሆኖ ያልፋል። "ዓኾይ ዓኾኾይ" የጎመን ምንቸት ውጣ የገንፎ ምንቸት ግባ በማለትም ችቦ ተሎኮሶ በየቤቱ በመዞር የምረቃ እና ለሚቀጥለው ዓመትም በሰላምና ደስታ እንዲሁም እድሜና ጤናን በመመኘት ይከወናል። የአደባባይ በዓል የሆነው የመስቀል በዓል በዝማሬ፣ በሆታና እልልታ የሚገለጽ ሲሆን፤ ወርሃ መስከረም እሸት አሽቶ አበቦች አብበውና ምድር ልዩ ልምላሜን ተላብሶ የሚታይ በመሆኑ ልክ በታሪኩ እንደሰፈረው የሰላም፣ የእውነትና የአንድነት በዓል መሆኑን በተግባር የሚታይበት ነው።
የሀመሯ እናት- የደስታ እንባ
Sep 11, 2025 1651
የሀመሯ እናት- የደስታ እንባ በጣፋጩ ሰለሞን (ከጂንካ) በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገኘው ሐመር ወረዳ የሐመር ብሔረሰብ ዘመን በተሻገሩ ባህላዊ ሥርዓቶች ይታወቃል። በዚህ አካባቢ ከሚዘወተሩትና በብዛት ከሚታወቁት ባህላዊ ሥርዓቶች መካከል “ኢቫንጋዲ እና ኡኩሊ” የተባሉ ባህላዊ ጨዋታዎች ይጠቀሳሉ። “ኡኩሊ”በሐመሮች ዘንድ በስፋት የሚታወቅ ባህላዊ ጨዋታ ሲሆን ለአቅመ አዳም የደረሰና ከብት ለመዝለል ዝግጁ የሆነ የሐመር ወጣት የሚጠራበት የማዕረግ ስም ነው፡፡ “ኡኩሊ” ከብት በሚዘለልበት ዕለት ሥርዓቱ በሚፈጸምበት ሥፍራ ላይ በቅርብም ይሁን በሩቅ ያሉ የወጣቱ ዘመዶች ተጠርተው የሚከናወን ባህላዊ ሥርዓት መሆኑ ይታወቃል። “ኢቫንጋዲ” ደግሞ በሐመሮች ዘንድ በስፋት የሚታወቅ ባህላዊ ጭፈራ ሲሆን ትርጉሙም “ኢቫን” ማለት “ ማታ” ሲሆን “ጋዲ” ማለት ደግሞ “ጭፈራ” ማለት መሆኑ ይነገራል። ኢቫንጋዲ በአዝመራና በደስታ ወቅት በሥራ የደከመን አእምሮና አካል ለማዝናናት ሲባል የሚከናወንና የሀመር ወጣቶች በጉጉት የሚጠብቁት ባህላዊ ጭፈራ ነው። በዚህ ባህላዊ ጨዋታ ላይ የሐመር ወጣት ወንዶችና ልጃገረዶች አምረውና ተውበው በጨረቃ ብርሃን ይጨፍራሉ። የኢቫንጋዲ ጭፈራ በሶስት ቀን አንድ ጊዜ በሐመር መንደሮች በምሽት ከጨረቃ ድምቀት ጋር አብሮ ይደምቃል። “በጨረቃ ብርሃን አየኋት በማታ ኢቫንጋዲው ቦታ” የተባለላቸው የሃመር ውብ ልጃገረዶችም ከጨረቃ ብርሃን ጋር ደምቀው የሚታዩበት ዕለት ይሆናል። በወጣትነታቸው በዚሁ ባህላዊ ሥርዓት ያለፉት የሀመሯ እናት- ወይዘሮ ባሎ ኡርጎ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ እናት ናቸው። በሐመር ወረዳ ዲመካ ከተማ የሚኖሩት ወይዘሮ ባሎ፤ በደሳሳ ጎጇቸው ሲያገኙ በልተው ሲያጡ ደግሞ ኩርምት ብለው ያሳለፉባቸው ጊዜያት እንዳሉ ያስታውሳሉ። በደሳሳ ጎጆ እየኖሩ ዝናብ ሲመጣ የጎርፍ፣ ብርድና ዶፉ ስጋት ላይ ጥሏቸው እንደኖሩ ያነሳሉ፤ በበጋ ወራት ደግሞ የሚነፍሰው ነፋስና ሀሩሩ ጸሃይ ይፈትናቸው እንደነበር ይናገራሉ። ከእለታት አንድ ቀን ወጣቶችና ጎልማሶች ጭምር ሰብሰብ ብለው መጥተው “ቤትዎን በነፃ ልናድስልዎት ነው ሲሉኝ አላመንኳቸውም ይላሉ። የእውነታችሁን ነው አልኳቸው? አዎን ቤትዎን አፍርሰን ልንሰራልዎት ነው” ብለው አረጋገጡልኝ በማለት ሁኔታውን በደስታ እንባ ታጅበው ያስታውሳሉ። በተባለው መሰረትም በክረምቱ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የቤታቸው እድሳት ተጀምሯል። የኢዜአ ሪፖርተር በስፍራው ተገኝቶ ወይዘሮ ባሎን ባነጋገራቸው ወቅት “ሰው በሚያስፈልገኝ ጊዜ ሰዎች ሁነው የተገኙ ወገኖቼ ችግሬን ለመፍታት በአካል ተገኝተዋል፤ በጣም ደስ ብሎኛል፤ የመኖርን ተስፋ እንድሰንቅ አድርገውኛል በማለት ደስታቸውን በእንባቸው ጭምር ታጅበው ገልጸዋል። የሀመሯ እናት ቤታቸው በፍጥነት ታድሶ የሚረከቡ፣ በቀጣይም አስፈላጊው እገዛና ድጋፍ የሚደረግላቸው መሆኑን የቤቱን እድሳት ያስጀመሩት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር አረጋግጠዋል። እንደ ወይዘሮ ባሎ፤ ያሉ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖችን የማገዝና የመደገፍ ሃላፊነት አለብን ያሉት ሃላፊው፤ የመረዳዳትና የመተጋገዝ ባህል ጎልቶ እንዲቀጥል ሁላችንም የድርሻችንን ልንወጣ ይገባል ብለዋል። የቢሮው የማኔጅመንት አባላትና ሰራተኞች ለወገኖቻቸውያላቸውን አለኝታነት በተግባር በማሳየታቸውም አመስግነዋል። የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ፤ የዘንድሮ የክረምት በጎ ፈቃድ ተቋማት፣ግለሰቦች፣ወጣቶችና አዛውንቶች ሳይቀር የተሳተፉበት እና የበርካቶችን ችግር መፍታት የተቻለበት መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ማኔጅመንት አባላትና ሰራተኞች የወይዘሮ ባሎን ቤት ለማደስ በመምጣታቸው አመስግነው፤ ለሌሎች ተቋማትም አርአያ የሚሆን የመልካምነት ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ በተያዘው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ቤቶችን ጨምሮ የዞኑን ማህበረሰብ ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም በዞኑ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖችን የመደገፍና ሰው ተኮር የልማት ስራዎችን በስፋት የማከናወን ተግባር በተጠናከረ መለኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል።