መጣጥፍ
የዘንድሮው የኮፓ አሜሪካ ዋንጫ ውድድር ልዩ አጋጣሚ
Jul 2, 2024 2686
በይስሐቅ ቀለመወርቅ የኮፓ አሜሪካ ዋንጫ ውድድር እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1916 በአርጀንቲና አስተናጋጅነት ተጀመረ። ዘንድሮ ደግሞ 48ተኛው የኮፓ አሜሪካ ዋንጫ ውድድር በአሜሪካን አዘጋጅነት እየተደረገ ይገኛል። በውድድሩ 16 አሰልጣኞች የተለያየ ሀገራትን ብሔራዊ ቡድን ይዘው የሚያሰለጥኑ ሲሆን፤ ከነዚህ ሰባቱ አርጀንቲናውያን አሰልጣኞች መሆናቸው የዘንድሮውን የኮፓ አሜሪካ ዋንጫ ውድድር ልዩ ያደርገዋል። በራሳቸው ሀገር ተወላጆች እየሰለጠኑ በኮፓ አሜሪካው እየተሳተፉ የሚገኙ ሀገራትን ስንመለከት ብራዚል በብራዚላዊው አሰልጣኝ ዶሪቫል ሲልቬስትር፤ ሜክሲኮ በሜክሲኳዊው ጃሚን ሎዛኖ፣ አዘጋጇ ሀገር አሜሪካ ደግሞ በአሜሪካዊው አሰልጣኝ ግሬግ ማቲውና አርጀንቲና ደግሞ በአርጀንቲናዊው ሊዮኔል ስካሎኒ እየሰለጠኑ ይገኛሉ። ፓናማ በዴንማርካዊው አሰልጣኝ ቶማስ ክርስቲያንሰን፤ ጃማይካ በአዬስላንዳዊው አሰልጣኝ ሂመር ሃልግሪምሰን፤ ካናዳ በአሜሪካዊው ጂሲ አለን፤ኢኳዶር በስፔናዊው ፍሊክስ ሳንቼዝ ፤ቦሊቪያ በብራዚላዊው አንቶኒዮ ካርሎስ እና ፔሩ በኡራጋዊው አሰልጣኝ በጆርጅ ፎሳቴ እየሰለጠኑ በኮፓ አሜሪካ በመሳተፍ ላይ ናቸው። በዘንድሮው ኮፓ አሜሪካ የአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝን ጨምሮ ሰባት አርጀንቲናውያን አሰልጣኞች ሰባት ሀገራትን እያሰለጠኑ ይገኛሉ። ለመሆኑ እነዚህ አርጀንቲናውያን አሰልጣኞች እነማናቸው?   ሊዮኔል ስካሎኒ፡- ይህ አርጀንቲናዊ አሰልጣኝ የአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድንን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2018 እያሰለጠነ የሚገኝ ሲሆን በ2021 የኮፓ አሜሪካን፤ በ2022 ደግሞ የዓለም ዋንጫን ከአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድን ጋር አሸንፏል። ዘንድሮም በኮፓ አሜሪካ ውድድር የአርጀንቲና ብሔራዊ ቡድንን ይዞ እየተሳተፈ የሚገኝ ሲሆን አርጀንቲና በምድብ ጨዋታዎቿ ካናዳ፣ ቺሊንና ፔሩን አሸንፋ ወደ ሩብ ፍፃሜ እንድትገባ አስችሏታል። ማርሴሎ ቤልሳ፡- የ68 ዓመት የዕድሜ ባለጸጋው አርጀንቲናዊ አሰልጣኝ የኡራጋይ ብሔራዊ ቡድንን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2023 ጀምሮ በማሰልጠን ላይ ይገኛሉ።   ዘንድሮም በኮፓ አሜሪካ ውድድር የኡራጋይ ብሔራዊ ቡድን የተሻለ እንቅስቃሴ እንዲያደርግ ያገዙት ሲሆን ፓናማን፣ ቦሊቪያንና አዘጋጇ ሀገር አሜሪካንን አሸንፎ ሩብ ፍፃሜ እንዲቀላቀል አስችለውታል። ፈርናንዶ ባቲስታ፡- በ53 ዓመት ዕድሜው ላይ የሚገኘው ይህ አርጀንቲናዊ አሰልጣኝ የቬንዙዌላ ብሔራዊ ቡድንን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2023 ጀምሮ በማሰልጠን ላይ ይገኛል።   ዘንድሮም በኮፓ አሜሪካ ውድድር የቬንዙዌላን ብሔራዊ ቡድንን ይዞ እየተሳተፈ ሲሆን፤ ቬንዙዌላ በምድብ ጨዋታዎቿ ኢኳዶርን፣ ሜክሲኮና ጃማይካን አሸንፋ ሩብ ፍፃሜ እንድትገባ አስችሏታል። ኔስተር ሎሬንዞ ፡- የ58 ዓመቱ አርጀንቲናዊ የኮሎምቢያ ብሔራዊ ቡድንን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2022 ጀምሮ እያሰለጠነ ይገኛል።   ዘንድሮም በኮፓ አሜሪካ ውድድር የኮሎምቢያን ብሔራዊ ቡድንን ይዞ ፓራጓይና ኮስታሪካን በምድብ ጨዋታ በማሸነፍ ኮሎምቢያ ሩብ ፍፃሜ እንድትገባ ያደረገ ሲሆን የመጨረሻ የምድብ ጨዋታውን ከብራዚል ጋር ያደርጋል። ሪካርዶ ጋርሲያ፡- የ66 ዓመቱ አንጋፋ አርጀንቲናዊ አሰልጣኝ ሪካርዶ ጋርሲያ የቺሊ ብሔራዊ ቡድንን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2024 ጀምሮ እያሰለጠኑ ይገኛሉ።   ዘንድሮም በኮፓ አሜሪካ ውድድር የቺሊ ብሔራዊ ቡድንን ይዘው በሚፈልጉት ርቀት መጓዝ አልቻሉም። በምድብ ጨዋታቸው ከካናዳና ፔሩ ጋር በተመሳሳይ 0 ለ 0 በሆነ ውጤት አጠናቀውና በአርጀንቲና 1 ለ 0 ተሸንፈው ከውድድሩ ውጪ ሆነዋል። ዳንኤል ጋርኔሮ፡- የ55 ዓመቱ አርጀንቲናዊ አሰልጣኝ የፓራጓይ ብሔራዊ ቡድንን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2024 ጀምሮ እያሰለጠነ ይገኛል። ዘንድሮም በኮፓ አሜሪካ ውድድር የፓራጓይ ብሔራዊ ቡድንን ይዞ እተሳተፈ የሚገኝ ሲሆን፤ በሚፈለገው ርቀት መጓዝ አልቻለም።   ከኮሎምቢያና ብራዚል ጋር ባደረጋቸው ሁለት የምድብ ጨዋታዎች ሽንፈትን በማስተናገዱ፤ከኮስታሪካ ጋር የሚያደርገው የመጨረሻ የምድብ ጨዋታ እየቀረው ከውድድሩ ውጪ ሆኗል። ጉስታቮ አልፋሮ፡- የ61 ዓመቱ አርጀንቲናዊ አሰልጣኝ የኮስታሪካ ብሔራዊ ቡድንን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2023 ጀምሮ በማሰልጠን ላይ ይገኛሉ።   ዘንድሮም በኮፓ አሜሪካ ውድድር የኮስታሪካን ብሔራዊ ቡድንን ይዘው በምድብ ጨዋታቸው በኮሎምቢያ ተሸንፈው ከብራዚል ጋር አቻ ተለያይተዋል። ወደ ሩብ ፍፃሜው ለማለፍ ከፓራጓይ ጋር የሚደርጉትን የመጨረሻ የምድብ ጨዋታ ማሸነፍና የኮሎምቢያና የብራዚልን የጨዋታ ውጤት መጠበቅ ግድ ይላቸዋል። በኮፓ አሜሪካ የዋንጫ ውድድር አርጀንቲና፣ ካናዳ፣ ቬንዙዌላ፣ ኢኳዶር፣ ኡራጋይ፣ ፓናማና ኮሎምቢያ ሩብ ፍፃሜውን የተቀላቀሉ ቡድኖች ናቸው። ኮሎምቢያ ከብራዚል፤ ኮስታሪካ ከፓራጓይ ከሌሊቱ 10 ሰዓት በሚያደርጉት ጨዋታ ደግሞ ሩብ ፍፃሜ የሚገባው ቀሪ አንድ ቡድን የሚለይ ይሆናል። በዘንድሮው የኮፓ አሜሪካ ዋንጫ ውድድር ሰባት አርጀንቲናውያን አሰልጣኞች ሰባት ሀገራትን እያሰለጠኑ እየተፋለሙበት ያለ ልዩ አጋጣሚ ፈጥሯል።    
የአውሮፓ ዋንጫን ለበርካታ ጊዜ ያነሱት አገራት እነማን ናቸው?
Jul 2, 2024 1775
(በሙሴ መለስ) እ.አ.አ 1960 የመጀመሪያው የአውሮፓ ዋንጫ (በቀድሞ አጠራሩ ኢሮፒያን ኔሽንስ ካፕ) የጀመረበት ዓመት ነው። በፈረንሳይ አስተናጋጅነት እ.አ.አ ከሐምሌ 6 እስከ 10 1960 በተካሄደው ውድድር የያኔዎቹ ሶቪየት ሕብረት፣ ቼኮዝሎቫኪያና ዩጎዝላቪያ ተሳትፈዋል። ሶቪየት ሕብረት (በአሁኑ ስያሜዋ ሩሲያ) በፍጻሜው ጨዋታ ዩጎዝላቪያን ስላቫ ሜትሬቬሊና ቪክቶር ፖንዴልኒክ ባስቆጠሯቸው ግቦች 2 ለ 1 በማሸነፍ ታሪካዊውን ዋንጫ አንስታለች። ከ64 ዓመት በፊት የተጀመረው የአውሮፓ ዋንጫ የዘንድሮውን ሳይጨምር 10 አገራት የውድድሩ አሸናፊ ሆነዋል። ጀርመንና ስፔን በተመሳሳይ ሶስት ጊዜ ዋንጫውን በማንሳት ስኬታማ የሆኑ አገራት ናቸው። ምዕራብ አውሮፓዊቷ ጀርመን እ.አ.አ በ1972፣ 1980 እና 1996 አህጉራዊውን ክብር ከፍ አድርጋ አንስታለች። ጀርመን ሁለት ጊዜ ዋንጫውን ያነሳችው ምዕራብ ጀርመንና ምስራቅ ጀርመን ከመዋሃዳቸው በፊት ነበር። ብሔራዊ ቡድኑ ካነሳቻው ዋንጫዎች በተጨማሪ 3 ጊዜ ለፍጻሜ ደርሶ ተሸንፏል። በደቡብ ምዕራብ አውሮፓ የምትገኘው ስፔን እ.አ.አ በ1964፣ 2008 እና 2012 በተካሄዱ ውድድሮች ዋንጫውን አንስታለች። 1 ጊዜ ለፍጻሜ ደርሳ ሽንፈትን አስተናግዳለች። ስፔን በሁለት ተከታታይ የአውሮፓ ዋንጫዎች ዋንጫ ያነሳች ብቸኛ አገር ናት። ጣልያንና ፈረንሳይ የአውሮፓ ዋንጫን ክብር ሁለቴ በመጎናጸፍ ይከተላሉ። የደቡብ ማዕከላዊ አውሮፓዊቷ አገር ጣልያን እ.አ.አ በ1968 እና 2020 ዋንጫውን አንስታለች። የ16ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ባለቤት ጣልያን በጀርመን አስተናጋጅነት እየተደረገ በሚገኘው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ በጥሎ ማለፉ በስዊዘርላንድ ተሸንፋ ከውድድሩ ውጪ መሆኗ የሚታወስ ነው። ሰማያዊዎቹ በሚል ቅጽል ስም በሚጠራው የፈረንሳይ ብሔራዊ ቡድን እ.አ.አ በ1984 እና 2000 የአውሮፓ ዋንጫን ወስዷል። በተጨማሪም ጣልያን 2 ጊዜ እና ፈረንሳይ 1 ጊዜ ለፍጻሜ ደርሰው ሽንፈት አስተናግደዋል። ፖርቹጋል፣ዴንማርክ፣ ኔዘርላንድ፣ግሪክ፣ ሩሲያና በቀድሞ አጠራሯ ቼኮዝሎቫኪያ( በአሁኑ ሰዓት ቼክ ሪፐብሊክና ስሎቫኪያ የሚጠሩት አገራት) በተመሳሳይ አንድ ጊዜ የአውሮፓ ዋንጫን አንስተዋል። ሩሲያ 3 ጊዜ እንዲሁም ቼኮዝሎቫኪያና ፖርቹጋል በተመሳሳይ 1 ጊዜ ለፍጻሜ ደርሰው ተሸንፈዋል። ከዚህ ውጪ ዋንጫ ባያነሱም የቀድሞ ዩጎዝላቪያ 2፣ ቤልጂየምና እንግሊዝ በተመሳሳይ 1 ጊዜ ለፍጻሜ ደርሰዋል። በጀርመን እየተካሄደ በሚገኘው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ አዲስ የዋንጫ ባለቤት ይገኝ ይሆን? ጥያቄው ሐምሌ 7 ቀን 2016 ዓ.ም ምላሽ ያገኛል።
በትውልድ ቅብብሎሽ ሀገርን ማጽናት
Jun 30, 2024 233
ከሀብታሙ ገዜ (ድሬዳዋ ኢዜአ ) ዕለቱ ደማቅና ውብ ነው፤ ድምቀቱ የአካባቢውን በረሃማነት ያስረሳል። ቢሆንም የፀሐዩ ግለት ይለያል_። ሰኔ 12 ቀን 2016 ዓ.ም የሁርሶ ቅጥር ጊቢው ውስጥ ነበርኩ። በስፍራው የተገኘሁት በመከላከያ ሰላም ማስከበር ማዕከል የሁርሶ የኮንቲንጀንት ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት ለስምንተኛ ዙር በመሠረታዊ ወታደርነት ሙያ ያሰለጠናቸውን ወታደሮች በማስመረቁ ይህኑን ሁነት ለመዘገብ ነው። ፀሐይ ከነ ቅደመ አያቶቿ ካለችበት ተጎልጉላ የወጣች ይመስል፤ አካባቢውን በተለየ መንገድ አጉናዋለች። የለበስኩትን ሸሚዝ አሸቀንጥሬ ወለሉ ላይ ብጥልም በላብ ከመጠመቅ አላዳነኝም ። በዚህ ሐሩር ውስጥ ከነ ሙሉ ወታደራዊ የደንብ ልብሳቸው በወታደራዊ ሰላምታ በሜዳው ደምቆ የሚታየው ወጣት አገር ጠባቂ መሠረታዊ ወታደሮች ለተመለከተ ሐረሩ ሳይሆን ቀዝቀዝ ያለ ውሽንፍር የተቀላቀለበት ዝናብ እያካፋ ይመስላል ። ድንገት የአካባቢውን ድባብ የለወጠ፤ በደም ስር ውስጥ የሚገባ መዝሙር ተለቀቀ፤ የአገር መከላከያ ሠራዊት መዝሙር መናኘት ያዘ። ታላላቅ የሠራዊታችን ጀነራሎች ፤ ሲቪል የለበሱ የምስራቅ ኢትዮጵያ አመራሮች ከተቀመጡበት ተነስተው ሙዝሙሩን አስተጋቡ። ቀና ብዬ የተመራቂ ወታደሮችን ገፅታ ቃኘው፤ በአብዛኞቹ ገፅታ ላይ ቁርጠኝነት ፤ ከከፊሎቹ የአይን ብሌኖች ውስጥ የእንባ ዘለላ እየተንቆረቆረ ነው፤ የማያቋርጥ ጅርት--- እስኪበቃኝ አነባሁ፤ አልወጣልህ አለኝ፤ መዝሙሩ እንዳለቀ ወደ ተመራቂ ወታደሮች ስፍራ አመራሁ። ቆራጥነት ፣ ጀግንነት፣ ትህትና ከድርጊትና ከአንደበታቸው ይፈሳል፤ ካሜራዬን ደቅኜ ከጥቂቶቹ ጋር አወጋሁ፤ ለአገር ሉአላዊነት ፤ ለአገር ነፃነት፤ ለህዝባችን ዘላቂ ሰላም እና ዕድገት ህይወታችንን ለመስጠት ተዘጋጅተናል አሉኝ። የአገር መከላከያ ሠራዊትን መቀላቀል የኛ የወጣቶች ኃላፊነት ነው፤ አባቶች በከፈሉት መስዕዋእት ለኛ ያስረከቡንን አገር ጠብቀን ለቀጣዩ ትውልድ ማስረከብ የሚቻለው ሠራዊቱን በመቀላቀል ነው" ቀጠሉ፤ እንደ ጅረት በሚፈሰው የወጣት አንደበታቸው ። አገር የተሸመነችው በቅብብሎሽ ነው፤ አገር የሚፀናው ለአገር መስዕዋትነት ለመከፈል በቆረጠ ወጣት ትውልድ ነው፤ የሆነ ጥልቅ ስሜት ወረረኝ፤ ወጣትነት ሁሉንም መሆን የሚቻልበት ዕድሜ ነው፤ ወጣት ሁሉንም ከመውጣትና ከመሻገር የመጣ አመላካች ስያሜ መሆኑን በትክክል ተረዳሁ። ከመሠረታዊ ወታደሮች መካከል አንዱዓለም ባዘዘው ድንገት ከመድረኩ አካባቢ መሠረታዊ ወታደር ሳሙኤል ከዲር ጫጬ የሚል ስም ተጠራ። አንድ ቁመተ መለሎ ቀጭን ወጣት ሜዳው ላይ ከተጠቀጠቁት እኩዮቹ መሐል ተመዞና በወታደራዊ እርምጃ ተውቦ ወደ መድረኩ ተጓዘ። ሜዳው በታላቅ ጩኸት ደመቀ.... የደመቀው እልልታና ጩኸት መነሻው መሠረታዊ ወታደር ሳሙኤል ከዲር በሰላም ማስከበር የሁርሶ የአጭር ኮርስ ዕጩ መኮንኖች ትምህርት ቤት አዛዥ የኮሎኔል ከድር ጫጬ ልጅ በመሆኑ ነው። ይሄም ብቻ አይደለም ኮሎኔል ከድር ወደ መደረኩ በወታደራዊ ሰላምታ እየተመመ ለሚገኘው ልጃቸው ልዩ ስጦታ በአደባባይ ለመስጠት በመዘጋጀታቸው ጭምር የተፈጠረ ነው። አባት ያዘጋጁትን ሽልማት ለዕለቱ የክብር እንግዳ ለሌተናል ጀነራል ሐጫሉ ሸለመ አስረከቡ፤ መሠረታዊ ወታደሩ በመከላከያ ህብረት የሰው ሃብት አመራር ዋና መምሪያ ኃላፊ ለሌተናል ሀጫሉ ሸለመና ለአባቱ ወታደራዊ ሰላምታ በማቅረብ እና ጎንበስ ብሎ በመሳም የተዘጋጀውን ሽልማት ተቀበለ፤ የሁሉም ታዳሚ አይኖች ወደ ትዕይንቱ ተጎለጎሉ፤ ወታደሩ ሽልማቱን ከታሸገው ከረጢት ውስጥ ፈልቅቆ ለመላው ታዳሚ አሳየ፤ በፍሬም የተለበደ የእናት ኢትዮጰያ የተዋበ ካርታ!!!! ጩኸቱ ይበልጥ ቀጥሎ ልዩ መንፈስ ሜዳውን አደበበው። ሌተናል ሐጫሉ ሸለመ ገፅታቸውን ኩራት ፣ መመካትና ትልቅ ተስፋ አልብሷቸው አለፈ... የአገር ሉአላዊነትና ክብር ፀንቶ የሚቆየው በዚህ መንገድ እና ቅብብሎሽ ነው፤ የአገር ዋልታ የሆነው ወጣቱ ትውልድ በዚህ ታላቅ ሙያ ውስጥ በስፋት በመግባት ለአገር አለኝታ መሆኑን በተግባር እያረጋገጠ ይገኛል ፤ አገርም ህዝብም የሚፀናው በዚህ ፈለግና ቅብብሎሽ ነው .... በፍጥነት አይኖቼ አሻግረው አፈጠጡ፤ ባዘኑ ፤ ደልዳላው ወታደራዊ አቋማቸው ታየኝ፤ ተፈተለኩ ወደ አጠገባቸው። ኮሎኔል ከድር ጫጬ የሁርሶ አጭር 'ኮርስ' ዕጩ መኮንኖች ትምህርት ቤት አዛዥ ናቸው፤ በፈገግታ ተቀበሉኝ። እኔ አባቶቼ የሰጡኝን አገር ከነ ሙሉ ክብሯ ለልጄ አስረክቤያለሁ፤ ለ33 ዓመታት አገሬን በዚህ ሙያ በፍቅር አገልግያለሁ ፤ አሁን ወደ ጡረታ ዋዜማ እየተጓዝኩ ነው ። ትህትናቸው ፤ በዝግታ የሚናገሩት ቃላት ሰው ሰርስረው ይገባሉ፤ ያስደምማሉ። ግዙፍና ጠንካራ አቋማቸው 20 አመት እንኳ ያገለገሉ አይመስሉም። የአገር መከላከያ የአገር ኩራት ነው፤ እዚህ ተቋም ተቀላቅሎ አገሩን እንዲያገለግል ተስማምተን ነው ልጄ ሳሙኤል ወደ ሠራዊቱ የገባው። አገሬ ሉአላዊነቷ ሲከበር ህዝቤ ይከበራል፤ እኔም እከበራለሁ፤ ኢትዮጵያን ጠብቃት -ኢትዮጵያን በታማኝነት አገልግላት ብዬ ነው አደራዬን በአደባባይ ያስረከብኩት፤ ከኢትዮጵያ በላይ የምሰጠው ሌላ ውድ ስጦት የለኝም ይላሉ። ሰላሳ ሶስት ዓመታት ሙሉ በታማኝነት ለኢትዮጵያ ያለኝን ፍቅርና ኩራት በተግባር አሳይቻለሁ፤ ይህንን የማስቀጠል ኃላፊነት የልጄና የዘመኑ ወጣቶች ኃላፊነት ይሆናል፤ ለአፍታ ድምፃቸውን አቆሙና ቃና ብለው ወደ አዲሶቹ ወጣት ወታደሮች ተመለከቱ፤ መለስ አሉና ለኢትዮጵያውያን ወላጆች መልዕክት ሰደዱ። የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲረዳኝ የምፈልገው -ውትድርና ማለት እጅግ የላቀ ሙያ መሆኑን ነው፤ አገርን በታማኝነት መጠበቅ ማለት ነው። ወላጆች ልጆቻቸውን ወደ እዚህ ግዙፍ ተቋም ሲልኩ ኩራት ሊሰማቸው ይገባል፤ ወደ ሞት መላክ የሚመስላቸው ካሉ ስህተት ነው፤ ቀን ከደረሰ ሞት የትም ቢሆን የማይቀር ዕዳ ነው። ለህዝብና ለአገር የሚከፈል መስዕዋትነት ፀፀት የሌለው ኩራት ነው..... እውነት ነው፤ በሃሳብ የኋሊት ተንደረደርኩ፤ በተጋመደ ኢትዮጵያዊ ወኔና ጀግንነት አገርን ለማፅናት የተዋደቁቱ አያቶች-አባቶች -እናቶች ድቅን አሉብኝ። በክብር በኩራት ያለፀፀት አገርን ለማፅናት የከፈሉት ዋጋ ፈካብኝ። " እኔን -አንተን-እሱን-እሷን- እነሱን- እነዚያን- በጥቅሉ እ-ኛ-ን እንድንሆን ፤ ኢትዮጵያውያን እንድንሆን ዋጋ ከፍለዋል። " ...ሰው ተከፍሎበታል፤ ከደምና ከአጥንት " እንድትል ከያኒዋ!!! ከሃሳቤ መለስ ብዬ የኮሎኔል ከድርን ልጅ ፍለጋ ሜዳውን አሰስኩ። በትህትና ተቀብሎ ሃሳቡን አከፋለኝ፤ በአደራ በአደባባይ ስለ ተቀበላት አገር አጫወተኝ። የልጅነት ዕድሜውን በወታደራዊ ካንፕ ማደጉ፤ በሠራዊቱ ፍቅርና ክብካቤ መገመዱ ፤ ለመከላከያ ሠራዊት ፣ ለአየር ኃይል፣ በአዲስ ለተደራጀው ባህር ኃይል ...የተለየ ፍቅር አለው። ለኢትዮጵያ የሚከፈልን ዋጋ ከአባቱና ከአባቱ ባልደረቦች በታሪክና በተግባር ውስጡ ሰርጿል። " ዛሬ ኢትዮጵያን ከአባቴ ተረክቤያለሁ፤ አባቴ ኢትዮጵያን ጠብቃት ፤በታማኝነት አገልግላት ብሎ ሸልሞኛል፤ እኔ አደራውን በቁርጠኝነት እውጣለሁ፤ ቀና ብለን ደረታችንን ሞልተን እንድንጓዝ አባቶቻችን አገርን ጠብቀውና አፅንተው አስረክበውናል፤ የኔም ትውልድ እናት አገራችንን አፅንቶ ለቀጣዩ ትውልድ ያስረክባል---" እውነቱን ነው፤ አገር የትውልድ ቅብብሎሽ ውጤት ናት፤ በሚሰጥና በሚቀበል ፅናት ነው ፀንታ ያለችው። ያየሁትን ዘግኜ በጥቂቱ ለማሳየት የተጓዝኩበትን ይሄን ፈለግ የምቋጨው ከዕለቱ ተመራቂ መሠረታዊ ወታደሮች መካከል ወጣት አንዱዓለም ባዘዘው በሰደደው መልዕክት ነው፦ የኢትዮጵያ ህዝብ ለአገር ሠራዊት ያለውን ጥልቅ ፍቅርና ክብር አውቃለሁ፤ ለዚህ ህዝብ መስዋዕትነት መክፈል ያኮራል፤ ሠራዊታችን የተጣለበትን አገራዊ ታላቅ ኃላፊነት በታላቅ ድል የሚደመደመው ህዝባችን ያለውን የርስበርስ ፍቅርና አንድነት ጠብቆ ሲያፀና ነው። የህዝብ ፍቅርና አንድነት፤ መከባበርና ተነጋግሮ መግባባት ለኛ ለሠራዊት አባላት ተልዕኮ መሳካት ስንቅ ይሆናል አበቃሁ/        
በአውሮፓ ዋንጫ ለበርካታ ጊዜ የተሰለፉ ተጫዋቾች
Jun 26, 2024 422
(በሙሴ መለሰ) ከተጀመረ 64 ዓመት ያስቆጠረው የአውሮፓ ዋንጫ በርካታ ኮከብ ተጨዋቾችን አስመልክቶናል እያስመለከተንም ይገኛል። ፈረንሳይ እ.አ.አ በ1960 ባዘጋጀችው የመጀመሪያ የአውሮፓ ዋንጫ ታሪካዊዋንና የውድድሩን ቀዳሚ ግብ ያስቆጠረው የያኔዋ ዩጎዝላቪያ አጥቂ ሚላን ጋሊች፣ በውድደሩ ታሪክ የመጀመሪያውን ሀትሪክ የሰራው የምዕራብ ጀርመኑ አጥቂ ዲተር ሙለርና በአንድ ውድድር ላይ ሁለት ሀትሪክ የሰራው ፈረንሳዊው ኮከብ ሚሼል ፕላቲኒ ከቀደምት የውድድሩ ድምቀቶች መካከል ይጠቀሳሉ። በአውሮፓ ዋንጫ 14 ግቦች በማስቆጠር የውድድሩ የምንጊዜውም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ፖርቹጋላዊው ኮከብ ክርስቲያኖ ሮናልዶ፣ በ17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ 16 ዓመት ከ338 ቀናት በመሰለፍ አዲስ ክብረ ወሰን የጨበጠው ስፔናዊ ታዳጊ ላሚን ያማልና በዘንድሮው አህጉራዊ መድረክ በ38 ዓመት ከ289 ቀናት እድሜው ጣልያን ላይ ግብ በማስቆጠር በውድድሩ ታሪክ ኳስን ከመረብ ጋር ያገናኘው በእድሜ ትልቁ ተጫዋች የክሮሺያ ኮከብ ሉካ ሞድሪች ደግሞ ከቅርቦቹ ከዋክብት መካከል ይገኙበታል። በ23 ሴኮንድ ጣልያን ላይ ግብ በማስቆጠር በውድድሩ ታሪክ ፈጣኗን ግብ ከመረብ ጋር ያገናኘው አልባኒያዊው ኔዲም ባጅራሚ ሌላው አይረሴ ተጫዋች ነው። በዚህ ጽሁፍ የዘንድሮውን ጨምሮ በአውሮፓ ዋንጫ ለበርካታ ጊዜ የተሰለፉ ተጨዋቾች መረጃን ይዘን ቀርበናል። እስከ አሁን በተደረጉት የአውሮፓ ዋንጫ ውድድሮች ለበርካታ ጊዜ የተሰለፈው ፖርቹጋላዊ ኮከብ ክርስቲያኖ ሮናልዶ ነው። ሮናልዶ የተሰለፈበት ጨዋታ ብዛት 27 ነው። የፖርቹጋል ብሔራዊ ቡድን አምበል ሮናልዶ ፖርቹጋል በቀጣይ በሚኖራት የጥሎ ማለፍ ጨዋታ የያዘውን ክብረ ወሰን ያሻሽላል ተብሎ ይጠበቃል። የ39 ዓመቱ ተጨዋች በአህጉራዊው መድረክ የተጫወተበት ለአውሮፓ ዋንጫ ለማለፍ የተደረጉ የማጣሪያ ጨዋታዎች ጋር ተደምሮ በ71 ጨዋታዎች ላይ በመሰለፍ የቀዳሚነቱን ስፍራ ይዟል። የአውሮፓ ዋንጫ የማጣሪያ ውድድሮችን ጨምሮ በአህጉራዊው መድረክ 55 ጎሎችን ከመረብ ላይ ያሳረፈ ብቸኛ ተጫዋችም ነው። ሮናልዶ የዘንድሮውን ጨምሮ በስድስት የአውሮፓ ዋንጫዎች ላይ በመሳተፍ የመጀመሪያ ተጫዋች ሆኗል። በተጨማሪም ፖርቹጋል ተርኪዬን 3 ለ 0 ባሸነፈችበት የምድብ 6 ጨዋታ በ39 ዓመት ከ138 ቀናት እድሜው ኳስ በማቀበል በውድድሩ ታሪክ ለጎል የሚሆን ኳስን ያቀበለ በእድሜው ትልቁ ተጫዋች ክብረ ወሰን ባለቤት ሆኗል። በተጨማሪም በአውሮፓ ዋንጫ ሰባት ግቦችን አመቻችቶ ያቀበለ የመጀመሪያው ተጫዋች መሆንም ችሏል። ከክርስቲያኖ ሮናልዶ በመቀጠል በአውሮፓ ዋንጫ ብዙ ጊዜ የተሰለፈው ተጫዋች የቡድን አጋሩ ኬፕለር ላቬራን ደ ሊማ ፌሬራ (ፔፔ) ነው። ፔፔ ፖርቹጋል ከተርኪዬ ባደረገችው የምድብ ጨዋታ ላይ በውድድሩ ላይ ያደረገውን የጨዋታ ብዛት ወደ 21 ከፍ አድርጓል። ፖርቹጋላዊው የተከላካይ መስመር ተጫዋች ፔፔ አገሩ ከቼክ ሪፐብሊክ ጋር ባደረገችው የምድብ መክፈቻ ጨዋታ በ41 ዓመት ከ113 ቀናት እድሜው በጨዋታው ላይ በመሰለፍ በውድድሩ ላይ የተሳተፈ በእድሜው አንጋፋ ተጫዋች ክብረ ወሰንን ይዟል። የሀንጋሪ የቀድሞ ግብ ጠባቂ ጋቦር ኪራሊ እ.አ.አ በ2016 ፈረንሳይ ባስተናገደችው 15ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ሀንጋሪ ከቤልጂየም በጥሎ ማለፉ ስትጫወት በ40 ዓመት ከ86 ቀናት እድሜ በመሰለፍ ክብረ ወሰኑን ለስምንት ዓመታት ይዞ ነበር። በበርካታ ጨዋታዎች የተሰላፊነት ዝርዝር ውስጥ ሶስተኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አሁንም ፖርቹጋላዊው የ37 ዓመት አንጋፋ ተጫዋች ጆአ ሞቲኒሆ ነው። ሞቲኒሆ በዘንድሮው የፖርቹጋል የአውሮፓ ዋንጫ ስብስብ ውስጥ ባይካተትም ከዚህ ቀደም በነበረው የውድድሩ ተሳትፎ 19 ጊዜ ተጫውቷል። የጣልያን የቀድሞ የተከላካይ ክፍል መስመር ተጫዋችና ኮከብ ሊኦናርዶ ቦኑቺ፣ ጀርመናዊው የቀድሞ የአማካይ ተጫዋች ባስቲያን ሽዋይንስታይገርና ጀርመናዊው ማኑኤል ኖየር በተመሳሳይ 18 ጊዜ በመሰለፍ ቀጣዩን ደረጃ ይዘዋል። ማኑኤል ኖየር በጀርመን አስተናጋጅነት እየተካሄደ ባለው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ የአገሩ የግብ ጠባቂ ዘብ ነው። ጣልያናዊው ኮከብ ጆርጂዮ ኪዬሌኒ፣ የጣልያን የቀድሞ አንጋፋ ግብ ጠባቂ ጂያንሉዊጂ ቡፎንና ጀርመናዊው የአማካይ ተጫዋች ቶኒ ክሮስ በተመሳሳይ 17 ጊዜ በአውሮፓ ዋንጫው አገራቸውን ወክለው ተሰልፈዋል። በ17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ወደ ጥሎ ማለፉ የገባችው የውድድሩ አዘጋጅ አገር ጀርመን ስብስብ አባል የሆነው ክሮስ ቀጣይ በሚያደርገው ጨዋታ ደረጃውን የማሻሻል እድል አለው። ጣልያናዊያኖቹ ኮከቦች ሊኦናርዶ ቦኑቺና ጆርጂዮ ኪዬሌኒ እ.አ.አ በ2020 በ11 አገራት አዘጋጅነት በተካሄደው 16ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ባለቤት የሆነችው ጣልያን ስብስብ ውስጥ የነበሩ ተጨዋቾች ናቸው። ኔዘርላንዳዊው የቀድሞ ግብ ጠባቂ ኤድዊን ቫን ደር ሳር፣ ፖርቹጋላዊው ግብ ጠባቂ ሩዊ ፓትሪሲዮ፣ ስፔናዊው ኮከብ አንድሪያስ ኢኒዬሽታ፣ፈረንሳዊው የቀድሞ ተጫዋች ሊሊያን ቱራም፣ ስፔናውያኑ ጆርዲ አልባና ሴስክ ፋብሪጋዝ፣ ጀርመናዊው አንጋፋ ተጨዋች ቶማስ ሙለርና ክሮሺያዊው ኮከብ ሉካ ሞድሪች በተመሳሳይ በአውሮፓ ዋንጫ 16 ጊዜ የተሰለፉ ተጫዋቾች ናቸው። ፖርቹጋላዊው ፓትሪሲዮ፣ ጀርመናዊው ቶማስ ሙለርና ከውድድሩ የተሰናበተችው ክሮሺያ ተጫዋች ሉካ ሞድሪች በ17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ የተሳተፉ ተጫዋቾች ናቸው። ስፔናውያኑ ጆርዲ አልባና አንድሬስ ኢኒዬሽታ በአሁኑ ሰዓት በቅደም ተከተል ለጃፓኑ ክለብ ቪሴል ኮቤና ለአሜሪካዊው ኢንተር ሚያሚ ክለቦች እየተጫወቱ ይገኛሉ። 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ እስከ ሐምሌ 7 ቀን 2016 ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን በውድድሩ ላይ እየተሳተፉ ያሉ ተጫዋቾች የተሰለፉበትን የጨዋታ ብዛት ሊያሳድጉ ይችላሉ።  
ዕድሜ ጠገቡ አህጉራዊ የእግር ኳስ ውድድር
Jun 25, 2024 341
በይስሐቅ ቀለመወርቅ እንደ መነሻ ጊዜው እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር 1859 ነው። ይህ ዓመት የመጀመሪያው የደቡብ አሜሪካ የክሪኬትና የእግር ኳስ ቡድን የሆነው "ሊማ" የተባለው ክለብ ፔሩ ውስጥ የተመሰረተበት ነው። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1893 ደግሞ፤ የአርጀንቲና የእግር ኳስ ማኅበር ተመሰረተ። እነዚህ ሁለት ሁነቶች ከኮፓ አሜሪካ ውድድር ጅማሮ መጠንሰስ ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት አላቸው። ማኅበሩ ከተመሰረተ ከ17 ዓመት በኋላ አርጀንቲና፣ ቺሊና ኡራጋይን በማካተት አህጉራዊ ውድድር ለማዘጋጀት ጥረት አደረገች። ሆኖም ይህ ወድድር የማዘጋጀት ሀሳብ የደቡብ አሜሪካን እግር ኳስ በሚመራው ኮንሜቦል ዕውቅና ተሰጥቶት አልተመዘገበም። ነገር ግን እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1916 ከአርጀንቲና የነፃነት በዓል ጋር ተያይዞ አርጀንቲና፣ ቺሊ፣ ኡራጋይና ብራዚል የተካተቱበት የእግር ኳስ ውድድር አርጀንቲና አዘጋጀች። ይህ ውድድርም "ካምፒዎናቶ ሱዳሜሪካኖ ዴ ፉትቦል ( Campeonato Sudamericano de Football )" በሚል፤ አሁን ላይ "ኮፓ አሜሪካ" በሚል መጠሪያ የሚደረገው የመጀመሪያ ውድድር ተካሄደ። በአርጀንቲና አዘጋጅነት የተጀመረው ይኼ ውድድር፤ 108 ዓመታትን በማስቆጠር፤ ዘንድሮም ለ48ተኛ ጊዜ በሰሜን አሜሪካዋ ሀገር አሜሪካ እየተከናወነ ይገኛል። አሜሪካ ዘንድሮ ውድድሩን እንዴት አዘጋጀች? የኮፓ አሜሪካ ዋንጫ ውድድር እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር እስከ 1975 ድረስ "የደቡብ አሜሪካ የእግር ኳስ ሻምፒዎና" እየተባለ ይጠራ ነበረ ሲሆን፤ ከ1975 በኋላ ደግሞ "ኮፓ አሜሪካ" እየተባለ መጠራት ጀመረ። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1993 ደግሞ የደቡብ አሜሪካን ውድድር የሚመራው "ኮንሜቦልና"፤ የሰሜን፣ መከካለኛውና ካሪቢያን ሀገሮች ውድድርን የሚመራው "ኮንካካፍ" በጋራ ለመሥራት ስምምነት በማድረጋቸው፤ በደቡብ አሜሪካ ካሉ 10 ሀገሮች በተጨማሪ ከኮንካካፍ ሁለት ቡድን በማካተት ውድድሩ መደረግ ጀመረ። በዚህም እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2016 የኮፓ አሜሪካ 100ኛ ዓመት ሲከበር አሜሪካ ውድድሩን የማዘጋጀት ዕድል ያገኘች ሲሆን፤ ዘንድሮም ለሁለተኛ ጊዜ ውድድሩን በማዘጋጀት ላይ ናት። ሜክሲኮ ደግሞ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1999 በፓራጓይ ከተደረገው የኮፓ አሜሪካ ውድድር በስተቀር፤ ከ1993 እስከ 2016 ድረስ በተደረጉት የኮፓ አሜሪካ ውድድሮች በተደጋጋሚ ተሳትፋለች። የኮፓ አሜሪካ ውድድር በዚህ ብቻ ባለመወሰን ከኮንካካፍ ሀገራት በተጨማሪ፤ ከእስያ የእግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን ሀገራትም ቡድኖችን በማካተት ተሳታፊ አድርጓል። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1999 በሜክሲኮ አለመሳተፍ ምክንያት ጃፓን በውድድሩ የተሳተፈች የመጀመሪያዋ የእስያ ሀገር ስትሆን፤ በ2019 ኳታርና ጃፓን እንዲሁ በኮፓ አሜሪካ ተሳትፈዋል። የኮፓ አሜሪካን ውድድርን በማዘጋጀትና፤ ዋንጫ በማንሳት እነማን የበላይ ናቸው? የኮፓ አሜሪካ ውድድር ከተጀመረ 11 ሀገራት ውድድሩን ያዘጋጁ ሲሆን፤ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1975፣ በ1979 እና በ1983 ደግሞ በአንድ አገር ውድድሩ ሳይዘጋጅ አገራት በሜዳቸውና ከሜዳቸው ውጪ የደርሶ መልስ ጨዋታ በማድረግ ውድድሩን አከናውናዋል። የኮፓ አሜሪካን ውድድርን 9 ጊዜ በማዘጋጀት አርጀንቲና ቀዳሚ ስትሆን፤ ኡራጋይና ቺሊ 7 ጊዜ፤ ብራዚልና ፔሩ ደግሞ 6 ጊዜ በማዘጋጀት ይከተላሉ። የኮፓ አሜሪካን ዋንጫ በማንሳት ደግሞ አርጀንቲናና ኡራጓይ እኩል 15 ጊዜ ሲያነሱ፤ ብራዚል 9 ጊዜ ዋንጫ አንስታለች። የ2024 ኮፓ አሜሪካ ውድድር ምን ይመስላል? የዘንድሮው የኮፓ አሜሪካ ውድድር ባሳለፍነው ሰኔ 14/ 2016 ዓ.ም አርጀንቲናና ካናዳ ባደረጉት የምድብ አንድ ጨዋታ የተጀመረ ሲሆን፤ አርጀንቲና በጁሊያን አልቫሬዝና በላውታሮ ማርቲኔዝ ሁለት ጎሎች ካናዳን 2 ለ 0 አሸንፋለች። 16 ሀገራት በአራት ምድብ ተከፍለው እየተወዳደሩበት በሚገኘው የዘንድሮ ኮፓ አሜሪካ ውድድር፤ ከምድብ አንድ እስከ አራት ያሉት ሀገራት የመጀመሪያ ምድብ ጨዋታዎቻቸውን አድርገዋል። በዚህም ከምድብ አንድ ፔሩ እና ቺሊ 0 ለ 0 በሆነ ውጤት ጨዋታቸውን የፈፀሙ ሲሆን፤ በምድብ ሁለት ቬንዙዌላ ኢኳዶርን 2 ለ1 በሆነ ውጤት አሸንፋለች። በዚሁ ምድብ ሜክሲኮ የካሪቢያዋን ሀገር ጃማይካን 1 ለ0 በሆነ ውጤት ረታለች። አዘጋጇ ሀገር አሜሪካንና ኡራጋይን ባፋጠጠው ምድብ 3 ደግሞ፤አሜሪካ ቦሊቪያን 2 ለ 0 በሆነ ውጤት ስትረታ፤ ኡራጋይ ፓናማን በማክሲሚሊያኖ አራጆ፣ በዳርዊን ኑኔዝና፣ በማትያስ ቪና ጎሎች 3 ለ 1 አሸንፋለች። በመጨረሻው ምድብ አራት ደግሞ ኮሎምቢያ ፓራጓይን 2 ለ1 ስታሸንፍ፤ ብራዚል ከኮስታሪካ ጋር 0 ለ 0 የአቻ ውጤት በሆነ ውጤት የመጀመሪያ የምድብ ጨዋታዋን ፈፅማለች። የኮፓ አሜሪካ የምድብ ሁለተኛ ጨዋታ ዛሬ ሌሊት ይካሄዳል። በምድብ አንድ ፔሩና ካናዳ ከምሽቱ 7 ሰዓት ላይ ጨዋታቸውን ሲያደርጉ፣ ቺሊና አርጀንቲና ደግሞ ከሌሊቱ 10 ሰዓት ይጫወታሉ። የወቅቱ የኮፓ አሜሪካ አሸናፊ አርጀንቲና በዛሬው ጨዋታ ድል ከቀናት በውድድሩ ሩብ ፍጻሜውን የምትቀላቀል የመጀመሪያ አገር ትሆናለች። ውድድሩ ነገም ቀጥሎ ሲውል በምድብ ሁለት፤ ኢኳዶር ከጃማይካ ቬንዙዌላ ከሜክሲኮ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ። የኮፓ አሜሪካ ውድድር በ14 የአሜሪካ ከተሞች በሚገኙ 14 ስታዲየሞች እየተከናወነ ሲሆን፤ ውድድሩ አስከ ሐምሌ 7 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ ይቆያል።        
ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾች የበዙበት የአውሮፓ ዋንጫ
Jun 24, 2024 369
በይስሐቅ ቀለመወርቅ በዓለም እግር ኳስ ውስጥ ከሚጠቀሱ ትልቅ አህጉራዊ የእግር ኳስ ውድድሮች አንዱ የአውሮፓ ዋንጫ ነው። በዚህ ውድድር ላይ መሳተፍ የብዙ አውሮፓውያን ተጫዋቾች ምኞት ነው። በጀርመን አስተናጋጅነት እየተካሄደ ባለው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ከ219 ክለቦች የተወጣጡ 622 ተጫዋቾች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። ከተጨዋቾቹ መካከል በዘንድሮው የአውሮፓ ዋንጫ አፍሪካዊ የዘር ግንድ ያላቸው 58 ተጨዋቾች የተለያዩ የአውሮፓ ሀገራትን ወክለው በውድድሩ ተሳትፈዋል። ፈረንሳይ፣ ቤልጂየም፣ ስዊዘርላንድ፣ እንግሊዝ፣ ጀርመን፣ ፖርቹጋል፣ ጣልያን፣ ስፔን፣ ዴንማርክና ኦስትሪያ ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን ይዘው በ17ተኛው የጀርመን የአውሮፓ ዋንጫ የተሳተፉ ሀገራት ናቸው ። ከነዚህም ውስጥ 14 ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን በመያዝ ቀዳሚ የሆነችው ሀገር ፈረንሳይ ናት። ፈረንሳይ፡- በዘንድሮውም የአውሮፓ ዋንጫ ፈረንሳይ ያካተተቻቸውን ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾች ምልከታ ከብሔራዊ ቡድኑ ኮከብ ኪሊያን ኢምባፔ እንጀምራለን። ኢምባፔ የዘር ግንዱ ከአፍሪካ የሚመዘዝ ሲሆን ከካሜሮናዊ አባትና ከአልጄሪያዊት እናት ነው የተወለደው። ለፈረንሳይ ብሔራዊ ቡድንና ለሪያል ማድሪድ አብሮት የሚጫወተው ፌርላንድ ሜንዲ ደግሞ የዘር ግንዱ ከሴኔጋልና ጊኒ ቢሳው ይመዘዛል። ለጀርመኑ ባየርሙኒክ የሚጫወተው ዳዮት ኡፓሜካኖም እንዲሁ ትውልዱ ከጊኒ ቢሳው የዘር ሐረግ የሚመዘዝ ነው ። ለፈረንሳዩ ሌንስ በግብ ጠባቂነት እየተጫወተ የሚገኘው ብራይስ ሳምባ፤ የሪያል ማድሪዱ ኤድዋርዶ ካማቪንጋና የፒኤስጂው ኮሎ ሙዋኒ ደግሞ ትውልዳቸው ከዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ይመዘዛል። የሳውዲ አረብያው አል ኢትሃድ ተጫዋች ኢንጎሎ ኮንቴ፤የሊቨርፑሉ ኢብራማ ኮናቴና ለሞናኮ በአማካይ ሥፍራ እየተጫወተ የሚገኘው የሱፍ ፎፋና ደግሞ ትውልዳቸው ከማሊ ነው። የፒኤስጂው ኡስማን ዴምበሌም በአባቱ የማሊ ተወላጅ ሲሆን እናቱ ደግሞ ሞሪታኒያዊት ነች። ኦሬሊን ቹዌሚኒ ከካሜሮን፣ ጁል ኩንዴ ከቤኒን፣ ዊሊያም ሳሊባ ከካሜሮንና ብራድሌ ባርኮላ ከቶጎ ሌሎቹ ለፈረንሳይ ብሔራዊ ቡድን የሚጫወቱ ተጫዋቾች ናቸው። ቤልጂየም፡- ከፈረንሳይ በመቀጠል በአውሮፓ ዋንጫው 9 ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን በመያዝ ቤልጂየም በሁለተኛነት ትከተላለች። ከቼልሲ በውሰት ለሮማ የሚጫወተው ሮሜሎ ሉካኩ፤የሲቪያው ዶዲ ሉካባኪዮ፤ከኖቲንግሃም ፎረስት በውሰት ለሊዮን የሚጫወተው ኦሬል ማንጋላ፤ ለአስቶንቪላ የሚጫወተው ዩሪ ቲሌማንስና ከዎልፍስበርግ በውሰት ለኤሲ ሚላን የሚጫወተው አስተር ፍራንክስ ትውልዳቸው ከዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ይመዘዛል። ለጀርመኑ አርቢ ላይፕዚግ የሚጫወተው ሎይስ ኦፔንዳ እንዲሁ የዲሞክራቲክ ኮንጎና የሞሮኮ የዘር ግንድ አለው። ለኔዘርላንዱ ክለብ ፒኤስቪ አይንዶቨን የሚጫወተው ዡዋን ባካዮኮ ደግሞ በእናቱ ሩዋንዳዊ በአባቱ ኮትዲቯራዊ ነው። ለእንግሊዙ ክለብ ኤቨርተን የሚጫወተው አማዱ ኦናና ከካሜሮናዊ አባትና ከሴኔጋላዊ እናት ነው የተወለደው። የማንችስተር ሲቲው ዠርሚ ዶኩ ደግሞ ትውልደ ጋናዊ ተጨዋች ነው። ስዊዘርላንድ ፡- ስምንት ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን በመያዝ ሶስተኛ ደረጃ ላይ የምትቀመጠው ስዊዘርላንድ ናት። የማንችስተር ሲቲው ኢማኑኤል አካንጂና፤ የኤሲ ሚላኑ ኖአ ኦካፎር ትውልደ ናይጄሪያውያን ተጨዋቾች ናቸው። ለፈረንሳዩ ክለብ ሎሪዮ የሚጫወተው ዩቩን ናኖማና፤ የሞናኮው ብሬል ኢምቦሎ ደግሞ ትውልዳቸው ከካሜሮን ነው። ከሞኖኮ ለቼልሲ በውሰት እየተጫወተ የሚገኘው ዴኒስ ዛካርያ ደግሞ፤ ከዲሞክራቲክ ኮንጎ አባትና ከደቡብ ሱዳናዊ እናት ነው የተወለደው። የበርንሌዩ አጥቂ መሐመድ አምዱኒ፤ የዘር ግንድ ስንመለከት ከተርኪዬ አባትና ከቱኒዚያዊ እናት ይመዘዛል። የቦሎኛው ዳን ንዶዬ ደግሞ ከስዊዘርላንድ እናትና ከሴኔጋላዊ አባት ነው የተወለደው። ለቡልጋሪያው ሉዶጎሬትስ ራዝጋርድ የሚጫወተው ኩዋድዎ አንቲ ዱአህ ሲሆን፤ ትውልደ ጋናዊ ተጨዋች ነው። እንግሊዝ፡- ከስዊዘርላንድ በመቀጠል 6 ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን በመያዝ አራተኛ ደረጃ ላይ የምትገኘው እንግሊዝ ናት። ለአርሰናል የሚጫወተው የቀኝ ክንፍ ተጨዋች ቡካዮ ሳካና፤ የክርስቲያል ፓላሱ ኢቤርቺ ኢዜ፤ ትውልደ ናይጀሪያውያን ተጨዋቾች ናቸው። የሊቨርፑል ተጫዋች ጆ ጎሜዝ ደግሞ ከጋምቢያዊ አባትና ከእንግሊዛዊ እናት ነው የተወለደው። ቀሪዎቹን ተጨዋቾች ስንመለከት የማንችስተር ዩናይትዱ ኮቢ ሜይኑ ከጋና ፣ የክርስቲያል ፓላሱ የመሀል ማርክ ጌይ ከኮትዲቯር፣ የአስቶንቪላው ኢዝሪ ኮንሳ ከዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ትውልዳቸው ይመዘዛል። ጀርመን፡- ከእንግሊዝ በመቀጠል 5 ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን በመያዝ በአምስተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠችው ደግሞ ጀርመን ናት። ለሪያልማድሪድ የሚጫወተውና በ17ተኛው የአውሮፓ ዋንጫ የራሳቸው ቡድን ላይ ጎል ካስቆጠሩ ተጨዋቾች ቀዳሚ የሆነው አንቶኒዮ ሩዲገር አባቱ የዘር ሐረጉ ከአፍሪካ የሚመዘዝ ጀርመናዊ (Afro German) ሲሆን እናቱ የሴራሊዮን ተወላጅ ነች። ቀሪዎቹን ተጨዋቾች ስንመለከት የባየር ሙኒኩ ወጣት ኮከብ ጀማል ሙሲያላ ከናይጄሪያ፤የባየር ሌቨርኩዘኑ ጆናታን ታህ ከኮትዲቯር፤ ለአርቢ ላይፕዚግ የሚጫወተው ቤንጃሚን ሄንሪክስ ከጋና፣ እንዲሁም የባየር ሙኒኩ ሊሮይ ሳኔ ደግሞ ከሴኔጋል የዘር ግንዱ ይመዘዛል። ኔዘርላንድና ፖርቹጋል ፡- ከጀርመን በመቀጠል በተመሳሳይ 4 ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን በመያዝ በስድስተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡት ደግሞ ኔዘርላንድና ፖርቹጋል ናቸው። የአትሌቲኮ ማድሪዱ ሜምፊስ ዲፓይ፣ የባየር ሌቨርኩዘኑ ጀርሚ ፍሪምፖንግና ለአያክስ በአጥቂ ሥፍራ የሚጫወተው ብሪያን ብሮቤይ ትውልደ ጋናውያን ተጨዋቾች ናቸው። ለሊቨርፑል የሚጫወተው ኮዲ ጋክፖ ደግሞ በአባቱ ቶጎዋዊ በእናቱ ጋናዊ ነው። ለፖርቹጋል የሚጫወቱ ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን ስንመለከት ደግሞ ለፈረንሳዩ የፒኤስጂው ኑኖ ሜንዴዝ በትውልዱ አንጎላዊ ነው። በተመሳሳይ ለፖርቹጋል ብሔራዊ ቡድን አብሮት የሚጫወተው ራፋኤል ሊያው ከአንጎላዊ አባትና የሳኦቶሜ ፕሪንሲፔ ተወላጅ ከሆነችው እናቱ ነው የተወለደው። ቀሪዎቹን ለፖርቹጋል እየተጫወቱ የሚገኙ ተጨዋቾችን ስንመለከት ለዎልቭስ በቀኝ ተመላላሽና በቀኝ ክንፍ መስመር ላይ የሚጫወተው ኔልሰን ሴሜዶ ከኬፕ ቬርዴ፤ እንዲሁም ዳንኤሎ ፔሬራ ከኢኳቶሪያል ጊኒ የዘር ግንዳቸው ይመዘዛል። ጣልያን፣ ስፔን፣ ዴንማርክና ኦስትሪያ፡- ከኔዘርላንድ በመቀጠል በተመሳሳይ ሁለት ትውልደ አፍሪካውያን ተጨዋቾችን በየቡድናቸው በማካተት ደግሞ ጣሊያን፣ ስፔን፣ ዴንማርክና ኦስትሪያ ሰባተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል። ጣልያን ለሄላስ ቬሮና የሚጫወተው ትውልደ ናይጄሪያዊ ማይክል ፎሎራንሾና ትውልደ ግብፃዊውን የሮማ ተጫዋች ስቴፋን አል ሻራዊ በአውሮፓ ዋንጫው በቡድኗ ውስጥ አካታለች። ስፔን ደግሞ ከሞሮኳዊ አባትና ከኢኳቶሪያል ጊኒ እናት የተወለደውን የባርሴሎና የክንፍ መስመር ተጨዋች ላሚን ያማልንና ትውልደ ጋናዊውን የአትሌቲኮ ቢልባኦ ተጨዋች ኒኮ ዊሊያምስን በአውሮፓ ዋንጫ ቡድኗ ውስጥ በማካተት እየተወዳደረች ትገኛለች። ዴንማርክ በበኩሏ ከታንዛኒያዊ አባትና ከዴንማርካዊ እናት የተወለደውን የአርቢ ላይፕዚግ ተጨዋች የሱፍ ፖልሰንና ትውልደ ጋምቢያዊውን የቤኔፊካ የቀኝ ተመላላሽ አሌክሳንደር ባህን በቡድኗ አካታለች። የመጨረሻዋ ትውልደ አፍሪካዊ ተጨዋቾችን በቡድኗ ያካተተችው ሀገር ኦስትሪያ ስትሆን፤ ትውልደ ጋናዊውን የሌንስ ተጫዋች ኬቨን ዳንሶ፤ ከኬንያዊ አባትና ከኦስትሪያዊ እናት የተወለደውን የሜንዝ ተከላካይ ፍሊፕ ሙዌኔን በቡድኗ ይዛለች።                                                                
በአውሮፓ ዋንጫ አገራቸውን ውክለው የተጫወቱ አባትና ልጆች
Jun 23, 2024 446
በይስሐቅ ቀለመወርቅ ለመነሻ በእግር ኳሱ ዓለም የጣልያናውያኑ የማልዲኒ ቤተሰቦች የእግር ኳስ ተጨዋችነት ታሪክ ለሦስት ትውልድ የዘለቀ መሆኑ ይነገርለታል። የሴዛር ማልዲኒ ልጅ የሆነው ፓውሎ ማልዲኒ እንዲሁም የፓውሎ ማልዲኒ ልጆች ክርስቲያን ማልዲኒ እና ታናሽ ወንድሙ ዳንኤል ማልዲኒ ከአባት እስከ ልጅ፣ ከልጅ እስከ የልጅ ልጅ ለደረሰው የእግር ኳስ ተጨዋችነት ውርርስ ማሳያ ናቸው። ለዛሬም በአውሮፓ ዋንጫ ታሪክ ሀገራቸውን ወክለው የተጫወቱ አባትና ልጅ ተጨዋቾችን በወፍ በረር እንቃኛለን። ለዚህ ጽሁፍ ሁሉም የተጠቀምነት የአውሮፓዊያን ዘመን አቆጣጠር ነው። ዳኒ ብሊንድ እና ልጁ ዴሊ ብሊንድ (ኔዘርላንድ) ፡- እነዚህ ኔዘርላንዳውያን አባትና ልጅ በተለያየ ጊዜ አገራቸውን ወክለው እግርኳስ ተጫውተዋል።   በ62 ዓመቱ ላይ የሚገኘው ዳኒ ብሊንድ፤ በተጨዋችነት ዘመኑ በተከላካይ ሥፍራ የሚጫወት ሲሆን ለአገሩ ክለቦች ስፓርታሮተርዳም እና አያክስ ተጫውቷል። በአሰልጣኝነት ሕይወቱም የአያክስ እና የኔዘርላንድ ብሔራዊ ብድንን በረዳትና በዋና አሰልጣኝነት አሰልጥኗል። በ1992 በስዊድን፣ በ1996 ደግሞ በእንግሊዝ አስተናጋጅነት በተከናወነው የአውሮፓ ዋንጫ አገሩን ወክሎ ተጫውቷል። በ34 ዓመት ዕድሜው ላይ የሚገኘው ልጁ ዴሊ ብሊንድ ደግሞ በተከለካይና በአማካይ ተከላካይ ቦታ የሚጫወት ሲሆን ለአገሩ ክለቦች ለሆኑት ግሮኒገን እና አያክስ ተጫውቷል። በተጨማሪም ለእንግሊዙ ማንችስተር ዩናይትድ እና ለጀርመኑ ባየርሙኒክ ከተጫወተ በኋላ አሁን ለስፔን ክለብ ጂሮና እየተጫወተ ይገኛል። በ2020 በአስራ አንድ ሀገራት በተከናወነው የአውሮፓ ዋንጫ ለሀገሩ ኔዘርላንድ በመሰለፍ ተጫውቷል። ኢንሪኮ ቼሳ እና ልጁ ፌድሪኮ ቼሳ (ጣሊያን)፡- እነዚህ ሁለት ጣልያናውያን አባትና ልጅ ሲሆኑ ሀገራቸውን ጣልያንን በተለያዩ ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ውድድሮች ወክለው ተጫውተዋል።   በ53 ዓመቱ ላይ የሚገኘው ኢንሪኮ ቼሳ፤ በተጨዋችነት ዘመኑ ከጣሊያኖቹ ክለቦች ሳምፕዶሪያ፣ ፓርማና ፊዮረንቲና ጋር ዋንጫዎችን አሸንፏል። በ1996 ደግሞ በእንግሊዝ አስተናጋጅነት በተከናወነው የአውሮፓ ዋንጫ ሀገሩን በመወከል ለጣልያን ብሔራዊ ቡድን ተሰልፏል። የ26 ዓመት ልጁ ፍድሪኮ ቼሳ በበኩሉ አሁን ላይ ለጁቬንትስ በክንፍ ተጨዋችነትና በአጥቂነት እየተጫወተ ሲሆን፤ በጣልያን ብሔራዊ ቡድን ከ19 ዓመት በታች፣ ከ20 ዓመት በታችና ከ21 ዓመት በታች ተጫውቷል። ከ2018 ጀምሮ ለጣልያን ዋናው ብሔራዊ ቡድን መሰለፍ የጀመረ ሲሆን፤ በ2020 የተደረገውን የአውሮፓ ዋንጫ ከጣልያን ጋር አሸንፏል። በጀርመን አስተናጋጅነት እየተከናወነ በሚገኘው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ደግሞ፤ በሉቺያኖ ስፓሌቲ የቡድን ስብስብ ውስጥ በመካተት ለጣልያን ብሔራዊ ቡድን እየተጫወተ ይገኛል። ሰርጂዮ ኮንሲሳኦ እና ልጁ ፍራንሲስኮ ኮንሲሳኦ(ፖርቹጋል)፡- እነዚህ ሁለት ፖርቹጋላውያን አባትና ልጅ ሲሆኑ በተለያየ ጊዜ ሀገራቸውን በእግር ኳስ ወክለው ተጫውተዋል።   የ49 ዓመቱ ሰርጂዮ ኮንሲሳኦ በተጨዋችነት ዘመኑ የክንፍ ተጨዋች የነበረ ሲሆን በአምስት ከተሞች ለ10 ክለቦች ተጫውቶ አሳልፏል። በተለይ የሀገሩ ክለብ ከሆነው ፖርቶና ከጣልያኑ ላዚዮ ጋር የተለያዩ የዋንጫ ክብሮችን አግኝቷል። በብሔራዊ ቡድን ደረጃም ለፖርቹጋል የተጫወተ ሲሆን በ2000 በኔዘርላንድና በቤልጂየም አስተናጋጅነት በተከናወነው የአውሮፓ ዋንጫ ለሀገሩ ተሰልፎ ተጫውቷል። የ21 ዓመቱ ልጁ ፍራንሲስኮ ኮንሲሳኦ ደግሞ አሁን ላይ ለፖርቶ በክንፍ ተጨዋችነት እየተጫወተ ይገኛል። በብሔራዊ ቡድን ደረጃም ለፖርቹጋል ከ16 ዓመት በታች፣ ከ17 ዓመት በታች፣ ከ18 ዓመት በታችና ከ21 ዓመት በታች የተጫወተ ሲሆን፤ ከ2024 ጀምሮ ለፖርቹጋል ዋናው ብሔራዊ ቡድን እየተጫወተ ነው። በጀርመን አስተናጋጅነት እየተከናወነ በሚገኘው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ፤ በሮቤርቶ ማርቲኔዝ በሚሰለጥነው የፖርቹጋል የቡድን ስብስብ ውስጥ በመካተት እየተጫወተ ይገኛል። ጆርጅ ሀጂ እና ልጁ ኢያኒስ ሃጂ (ሮማንያ)፡- እነዚህ የሮማንያ የእግር ኳስ ተጨዋቾች አባትና ልጅ ሲሆኑ ሀገራቸው ሮማንያን በተለያዩ ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ውድድሮች ወክለው ተጫውተዋል።   የ59 ዓመቱ ጆርጅ ሀጂ በአጥቂ አማካይ ሥፍራ የተጫወተ ሲሆን በ1980ዎቹና፣ በ1990ዎቹ በዓለም ላይ አሉ ከሚባሉ ኮከብ ተጨዋቾች መካከል ስሙ ይነሳል። በተጨዋችነት ዘመኑም ለሪያልማድሪድና ለባርሴሎና ለሁለት ተቀናቃኝ ክለቦች ከተጫወቱ ተጨዋቾችም አንዱ ነው። ለሀገሩ ክለቦች ኮንስታንታ፣ ስፖርቱል ስቱዴንቴስ እና ስቲዋ ቡካሬስት የተጫወተ ሲሆን የጣልያኑ ክለብ ብሬስካ ካልሲዮ እና የቱርኩ ክለብ ጋላታስራይ ሌሎች የተጫወቱባቸው ክለቦች ናቸው። ከ1983 እሰከ 2000 ለሀገሩ ሮማንያ ተሰልፎ የተጫወተ ሲሆን፤ በ1984 በፈረንሳይ፤ በ1996 በእንግሊዝና በ2000 በኔዘርላንድና በቤልጂየም አስተናጋጅነት በተከናወነው የአውሮፓ ዋንጫ ለሀገሩ ተሰልፎ ተጫውቷል። የ25 ዓመት ልጁ ኢያኒስ ሀጂ የእሱን ፈለግ በመከተል ኳስ ተጨዋች የሆነ ሲሆን፤ እንደ አባቱ በአጥቂ አማካይ ሥፍራና በተጨማሪም በክንፍ ተጨዋችነት ይጫወታል ። በ16 ዓመቱ ለሮማንያው ክለብ ቪያትሮል ኮንስታንታ በመጫወት የጀመረ ሲሆን ለጣልያኑ ፌዮረንቲና፣ ለቤልጂየሙ ጌንክ እና ለስኮትላንዱ ሬንጀርስም ተጫውቷል። አሁን ላይ ለስፔኑ ክለብ አላቪስ በውሰት እየተጫወተ ሲሆን ለሮማንያ ዋናው ብሔራዊ ቡድን ከ2018 ጀምሮ እየተጫወተ ይገኛል። በጀርመን አስተናጋጅነት እየተከናወነ በሚገኘው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ደግሞ በሮማንያ ብሔራዊ ቡድን በመካተት እየተጫወተ ነው። ፒተር ሹማይክልና ካስፐር ሹማይክል (ዴንማርክ )፡- እነዚህ ሁለት ዴንማርካውያን አባትና ልጅ በተለያየ ጊዜ ሀገራቸውን በእግር ኳስ ወክለው ተጫውተዋል።   የ60 ዓመቱ ፒትር ሹማይክል በግብ ጠባቂነት ለስምንት ዓመታት በማንችስተር ዩናይትድ የተጫወተበት ስኬታማ የክለብ ቆይታው ነበር። በተለይም በ1999 ከማንችስተር ጋር የፕሪሚየርሊግ፣ የኤፌካፕና የአውሮፓ ሻምፒዎንስ ሊግ ዋንጫ ያነሳበት በክለብ ተጨዋችነት ጊዜው የጎላ ስኬቱ ነው፤ ከ1987 እስከ 2001 ለዴንማርክ ብሔራዊ ቡድን ተጫውቷል። በ1988 በያኔዋ ምዕራብ ጀርመን አስተናጋጅነት በተከናወነው የአውሮፓ ዋንጫ እና በ2000 በኔዘርላንድና በቤልጂየም አስተናጋጅነት በተደረገው የአውሮፓ ዋንጫ ለሀገሩ ዴንማርክ ተሰልፎ ተጫውቷል። የ37 ዓመት ዕድሜ ላይ የሚገኘው ልጁ ካስፐር ሹማይክል ልክ እንደ አባቱ በግብ ጠባቂነት የሚጫወት ሲሆን ከተጫወተባቸው ክለቦች መካከል ከሌስተር ሲቲ ጋር ያሳለፈው ጊዜ የሚረሳ አይደለም። በ2015 ከሌስተር ጋር የእንግሊዝ ፕሪሚየርሊግ ዋንጫን ያነሳበት ተጨዋቹ በክለብ እግር ኳስ ተጨዋችነቱ ካሳለፋቸው ጊዜያት ቀዳሚው እንደሆነ ይናገራል። ከ2013 ጀምሮ ለዴንማርክ ዋናው ብሔራዊ ቡድን ተሰልፎ እየተጫወተ ሲሆን በ2020 በአስራአንድ ሀገራት በተከናወነው የአውሮፓ ዋንጫ፤ ለሀገሩ ዴንማርክ በመሰለፍ ተጫውቷል። ሊሊያን ቱራምና ልጁ ማርኮስ ቱራም( ፈረንሳይ)፡- እነዚህ ፈረንሳውያን አባትና ልጅ የእግር ኳስ ተጨዋቾች ሀገራቸው ፈርንሳይን በተለያዩ ዓለም አቀፍ የውድድር መድረኮች ወክለው ተጫውተዋል።   የ52 ዓመት ዕድሜ ላይ የሚገኘው ሊሊያን ቱራም፤ እግር ኳስ መጫወት የጀመረው ለፈርንሳዩ ክለብ ሞናኮ በመጫወት ነበር ። የጣልያኖቹ ክለቦች ፓርማና ጁቬንትስ እንዲሁም የስፔኑ ክለብ ባርሴሎና ቀሪ የተጫወተባቸው ክለቦች ናቸው ። በ1998 ሀገሩ ፈረንሳይ አዘጋጅታ በነበረው 16ኛው የዓለም ዋንጫ በግማሽ ፍፃሜ ከክሮሽያ ጋር ስትገናኝ ሁለት ጎሎችን በማስቆጠር ሀገሩ ወደ ፍፃሚ ገብታ የዋንጫ ባለቤት እንዲትሆን አድርጎል። በ2000 ለመጀመሪያ ጊዜ በኔዘርላንድና ቤልጂየም ጣምራ አዘጋጅነት በተከናወነው የአውሮፓ ዋንጫ፤ ለሀገሩ ፈረንሳይ ተሰልፎ በመጫወት ዋንጫ አንስቷል። በ26 ዓመት ዕድሜ ላይ የሚገኘውና ለጣልያኑ ክለብ ኢንተር ሚላን የሚጫወተው ልጁ ማርኮስ ቱርሃም ደግሞ፤ ለፈረንሳይ ብሔራዊ ቡድን በተለያየ የዕድሜ ደረጃ ተጫውቷል። ለፈረንሳይ ከ17 ዓመት በታች፣ ከ18 ዓመት በታች፣ ከ19 ዓመት በታችና ከ20 ዓመት በታች ተሰልፎ ተጫውቷል። ከ2020 ጀምሮ ለፈረንሳይ ዋነው ብሔረዊ ቡድን እየተጨወተ ይገኛል። በጀርመን አስተናጋጅነት እየተከናወነ በሚገኘው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ደግሞ፤ በፈረንሳይ ብሔራዊ ቡድን ውስጥ በመካተት እየተጫወተ ይገኛል።
በአውሮፓ ዋንጫ ታሪክ ሀትሪክ የሰሩት ሰባት ተጫዋቾች 
Jun 21, 2024 465
አንድ እግር ኳስ ተጫዋች ለክለብህ ነው ወይስ ለአገርህ ግብ ብታስቆጥር ይበልጥ የሚያስደስትህ? ተብሎ ቢጠየቅ ለአገሬ የማስቆጥረው ግብ ትልቅ ዋጋ እሰጠዋለሁ ብሎ እንደሚመልስ አያጠራርጥርም። ተጫዋቾች ለአገራቸው የመጀመሪያ ጨዋታቸውን አደረጉ፣ በብሔራዊ ቡድን መለያ የመጀመሪያ ግባቸውን አስቆጠሩ መባል ትልቅ ደስታና ክብር እንዲሰማቸው ያደርጋል። ለአገራቸው ግብ በሚያስቆጥሩበት ወቅት አንዳንዴ በእንባ ሌላ ጊዜም በፈንጠዝያና በደስታ ስሜታቸውን ይገልጻሉ። በዚህም የተደበላለቀ ስሜት ውስጥ ይገባሉ። ተጫዋቾች በዓለም ዋንጫና ሌሎች አህጉራዊ ውድድሮች አገራቸውን ወክለው መጫወት ትልቁ ሕልማቸው ነው። በእነዚህ ውድድሮች በአሰልጣኞች ጥሪ ሲደረግላቸው የመደሰትና የመጓጓት፣ ሳይካተቱ ሲቀሩ ደግሞ የማዘን ስሜት ይሰማቸዋል። የመጀመሪያ ዙር ጥሪ ውስጥ ተካተው መጨረሻ ላይ የሚቀነሱ ተጫዋቾችም በቡድናቸው አለመካተታቸው ያስቆጫቸዋል። በዓለም እግር ኳስ ውስጥ ከሚጠቀሱ ትልቅ ውድድሮች አንዱ የአውሮፓ ዋንጫ ሲሆን በዚህ ውድድር ላይ መሳተፍ የብዙ አውሮፓውያን ተጫዋቾች መሻት ነው። በጀርመን አስተናጋጅነት እየተካሄደ ባለው የአውሮፓ ዋንጫ ከ219 ክለቦች የተወጣጡ 622 ተጫዋቾች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። ይህ ግዙፍ ስፖርታዊ መድረክ ከተጀመረ 64 ዓመቱን ደፍኗል። የመጀመሪያው የአውሮፓ ዋንጫ (በቀድሞ አጠራሩ ኢሮፒያን ኔሽንስ ካፕ) የተካሄደው እ.አ.አ በ1960 ነው። አዘጋጇ አገር ፈረንሳይ ነበረች። በውድድሩ ላይ አዘጋጇ አገርን ጨምሮ የቀድሞዎቹ ሶቪየት ሕብረት፣ ዩጎዝላቪያና ቼኮዝሎቫኪያ ተሳትፈዋል። የዩጎዝላቪያው አጥቂ ሚላን ጋሊች የአውሮፓ ዋንጫ የመጀመሪያ ግብ ያስቆጠረ ተጫዋች ነው። ሶቪየት ሕብረት ባነሳችው ዋንጫ ፈረንሳያዊው ፍራንስዋ ሁት፣ የሶቪየት ሕብረቶቹ ቫለንቲን ኢቫኖቭና ቪክቶር ፖንዴልኒክ እንዲሁም የዩጎዝላቪያዎቹ ሚላን ጋሊችና ድራዛን ጄርኮቪች በተመሳሳይ ሁለት ግቦችን በማስቆጠር በጋራ የውድድሩ ኮከብ ግብ አግቢ ሆነዋል። በ1960 አንድ ብሎ የጀመረው የአውሮፓ ዋንጫ ዛሬ 17ኛው ላይ ደርሷል። ከዚህ ቀደም በተደረጉ 16 የአውሮፓ ዋንጫ ጨዋታዎች ላይ ስምንት ተጫዋቾች በአንድ ጨዋታ ሶስት ግቦችን በማስቆጥር ሀትሪክ ሰርተዋል። በውድድሩ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ሀትሪክ የተሰራው እ.አ.አ በ1976 የቀድሞዋ ዩጎዝላቪያ ባዘጋጀችው 5ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ነው። በግማሽ ፍጻሜው የያኔዋ ምዕራብ ጀርመን ዩጎዝላቪያን 4 ለ 2 ስታሸንፍ ዲተር ሙለር ሶስት ግቦች በማስቆጠር ስሟን በደማቅ ቀለም አጽፏል። ሙለር በውድድሩ በአጠቃላይ 5 ግቦችን በማስቆጠር ኮከብ ግብ አስቆጣሪ በመሆን አጠናቋል። ቀጣዩ የሀትሪክ ተረኛ ሌላኛው የጀርመን የቀድሞ ተጫዋች ክላውስ አሎፍስ ነው። አሎፍስ እ.አ.አ 1980 ጣልያን ባዘጋጀችው 8ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ምዕራብ ጀርመን ኔዘርላንድን 3 ለ 2 ስታሸንፍ ሶስት ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ተጫዋቹ ኔዘርላንድ ላይ በሰራው ሀትሪክ የውድድሩ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኗል። ፈረንሳይ እ.አ.አ በ1984 አዘጋጅታ ራሷ በወሰደችው 7ኛው የአውሮፓ ዋንጫ የቀድሞ የፈረንሳይ ኮከብ አጥቂ በሁለት ጨዋታዎች ሀትሪክ በመሥራት በውድድሩ አዲስ ታሪክ ጽፏል። ሚሼል ፕላቲኒ ፈረንሳይ ቤልጂየምን 5 ለ 0 እንዲሁም ዩጎዝላቪያን 3 ለ 2 ስትረታ በተመሳሳይ ሶስት ግቦችን አስቆጥሯል። ፕላቲኒ በውድድሩ 5 ጨዋታዎችን አድርጎ 9 ግቦችን በማስቆጠር የኮከብ አግቢነት ሽልማቱን ወስዷል። የቀድሞው አጥቂ ከፓርቹጋላዊ ክርስቲያኖ ሮናልዶ በመቀጠል የአውሮፓ ዋንጫ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ዝርዝር ላይ ሁለተኛ ደረጃን ይዟል። ምዕራብ ጀርመን እ.አ.አ በ1988 ባዘጋጀችው 8ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ኔዘርላንዳዊው ኮከብ ማርኮ ቫን ባስተን አገሩ እንግሊዝን ስታሸንፍ 3 ግቦችን በማስቆጠር ሀትሪክ ሰርቷል። ቫንባስተን ኔዘርላንድ ብቸኛውን የአውሮፓ ዋንጫን እንድታነሳ ቁልፍ አስተዋጽኦ ያበረከተ ተጫዋች ሲሆን በውድድሩ ሶቪየት ኅብረት ላይ በፍጻሜው ጨዋታ ላይ ያስቆጠረውን ግብ ጨምሮ በአጠቃላይ 5 ግቦችን ከመረብ ጋር በማዋሃድ የኮከብ አግቢነት ሽልማቱን አግኝቷል። በአውሮፓ ዋንጫ ቀጣዮቹን ሀትሪክ ሰሪዎች ለማግኘት 12 ዓመት መጠበቅ ግድ ብሏል። እ.አ.አ በ2000 ቤልጂየምና ኔዘርላንድ በጣምራ ባዘጋጁት 11ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ሁለት ተጫዋቾችን በተመሳሳይ በአንድ ጨዋታ ሦስት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል። የክንፍ መስመር ተጫዋቹ ሰርጂዮ ኮንሴሳዎ ፖርቹጋል ጀርመንን 3 ለ 0 ባሸነፈችበት ጨዋታ ሀትሪክ ሰርቷል። ሌላኛው በውድድሩ ላይ ሀትሪክ የሰራው ተጫዋች ኔዘርላንዳዊው ኮከብ ፓትሪክ ክላይቨርት ነው። በጥሎ ማለፍ ጨዋታ ኔዘርላንድ ዮጎዝላቪያን 6 ለ 1 ስትረመርም ክላይቨርት ሶስት ግቦችን ከመረብ ላይ አሳርፏል። ክላይቨርት በውድድሩ ላይ ከሰርቢያዊው ሳቮ ሚሎሶቪች ጋር በተመሳሳይ አምስት ግቦችን በማስቆጠር በጋራ የኮከብ ግብ አግቢነት ሽልማቱን ወስዷል። ለመጨረሻ ጊዜ በአውሮፓ ዋንጫው ሀትሪክ የሰራው የቀድሞው የስፔን ኮከብ ዴቪድ ቪያ ነው። ቪያ እ.አ.አ በ2008 ኦስትሪያና ስዊዘርላንድ በጣምራ ባዘጋጁት 13ኛው የአውሮፓ ዋንጫ ስፔን ሩሲያን 4 ለ 1 ስታሸንፍ ሶስት ግቦችን ከመረብ ጋር አገናኝቷል። ስፔናዊው ኮከብ በአጠቃላይ በውድድሩ 4 ግቦችን በማስቆጠር የኮከብ አግቢ ሽልማቱን ወስዷል። ዴቪድ ቪያ ለስፔን ባደረጋቸው 98 ጨዋታዎች 59 ግቦችን በማስቆጠር የአገሩ የምንጊዜም ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ነው። የአውሮፓ ዋንጫ ከዴቪድ ቪያ በኋላ ሀትሪክ የሰራ ተጫዋች ማግኘት የናፈቀው ሲሆን በውድድሩ በአንድ ጨዋታ ሶስት ግብ ያገባ ተጫዋች ከታየ 16 ዓመታት አልፈዋል። በጀርመን እየተካሄደ ባለው 17ኛው የአውሮፓ ዋንጫ እስከ አሁን በተደረጉ 18 ጨዋታዎች 47 ግቦች ተቆጥረዋል። በውድድሩ ላይ እስከ አሁን ሀትሪክ የሰራ ተጫዋች የለም። በአውሮፓ ዋንጫ በሚደረጉ ቀጣይ 33 ጨዋታዎች ሀትሪክ የሚሰራ ተጫዋች ይገኝ ይሆን? መልሱን ከጨዋታዎቹ።                
መከላከያ ሠራዊት-የኢትዮጵያ ሉዓላዊነት የመጨረሻ ምሽግ
Jun 12, 2024 685
በዋጋ ለተቀበሉት ኪዳን ያለጥርጥር መታመን፣ ለእውነትና ለፍትሕ በርትዕ መቆም የአላማ አይነተኛ ፍቺ ነው። የዚህም ነጸብራቅ ደግሞ ሰራዊት ነው። የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማዕከል የካቲት 1993 ያሳተመው አማርኛ መዝገበ ቃላት ሰራዊት የሚለውን ቃል “ለአንድ አላማ በአንድ ቡድን ውስጥ የተሰባሰበ ብዙ ህዝብ” የሚል ፍቺ ሰጥተቶታል። ከጥሬ ቃላቱ ጥቅል ትርጉም እንደምንረዳው ሰራዊት ለህዝቦች ሉዓላዊነት እና አንድነት በአላማ የቆመ የአሸናፊነትን አርማን ስንቁ በማድረግ የሚጓዝ የህዝብ ልጅ ማለት ነው። በዚህ አላማና ርዕይ የተሰራው የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትም የኢትዮጵያን የግዛት አንድነትና የዜጎቿን ደኅንነት የማረጋገጥ ታሪካዊ ኃላፊነት የተሸከመ ህዝባዊ ሰራዊት ነው። የመከላከያ ሰራዊት ኢትዮጵያ በዘመናት ውስጥ የገጠሟትን እና የሚገጥሟትን ፈተናዎች ድል በማድረግ ከፍታዋን አስጠብቆ የኖረ እና የሚኖር ሰራዊት ነው። የሰራዊቱ ግብና ተልዕኮ የሉዓላዊነት ሥጋት፤ የህዝብ ሠላምና ደህንነት እንቅፋት የሆኑ ችግሮችን በደም ዋጋ በማስከበር የህዝብ የሃገር ሉአላዊነትን ማስቀጠል ነው። የኢፌዴሪ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በአንድ ወቅት ስለሰራዊቱ ሲናገሩ መከላከያ ሰራዊት ያለ ሰላም እንዳይደፈርስ የሚጠብቅ፣ የጠፋን ሰላም ለማምጣት የሚተጋ፣ የመጣ ሰላምን ለማጽናት የሚሰራ ዋነኛ ዓላማውም ሰላምን ማስፋትና የሃገር ብልጽግናን ባልተቋረጠ መንገድ እውን ማድረግ ብቻ ነው ማለታቸው ይታወሳል። ዘመን በማያዝለው ልጆቿ ክንድ ጠላቶቿን ድል እየነሳች በአሻናፊነት የጸናችው ኢትዮጵያ ጀግናው ሰራዊቷ ከራሷ አልፎ ለጎረቤት ሀገራት ብሎም በአለም አቀፍ ወታደራዊ ተልዕኮዎች ብቃቱንና ሰላም አስከባሪነቱን ያስመሰከረ መሆኑም ይታወቃል። ለዚህም ከ60 ዓመታት በፊት የሰራዊቱን ታሪካዊ ጀግንነት ያስመሰከረው የኮሪያ ጦርነት፣ የኮንጎና ሩዋንዳ ዘመቻ የጎረቤት ሀገራት ሶማሊያ እና ሱዳን ሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች ሕያው የታሪክ ምስክሮ ናቸው ። ሰራዊቱ በተሠማራባቸው የግዳጅ ቀጣናዎች ከጠላት ነፃ ያወጣውን ማህበረሰብ በመንከባከብ፣ በጉልበቱ የልማት ሥራዎችን ማገዝም የሰርክ ልማዱ ነው። የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በአህጉር አቀፍና ቀጣናዊ የተልእኮ ስፍራዎች ያበረከታቸው ሰው ተኮር ድጋፎች የሰራዊቱን አለኝታነት በገሃድ የሚናገሩ ሀቆች ናቸው። ከራስ በፊት ለህዝብና ለሀገር በሚል መርህ የታነፀው ሠራዊቱ ምን ጊዜም አሸናፊና በየአውደ ውጊያው ሁሉ ባለድልም ነው። በየጊዜው የሚነሱ ጸረ ሰላም ሃይሎችን በመደምሰስ የኢትዮጵያን ልማትና አንድነት የሚያስጠብቀው ይህ ሰራዊት አሁንም በአሸባሪው ሸኔና በፅንፈኛ ሃይሎች ላይ የማያዳግም እርምጀ እየወሰደ ይገኛል። ሠራዊቱ ከየአካበቢው የህብረተሰብ ክፍልና ፀጥታ ሃይሎች ጋር በመቀናጀት አስተማማኝ ሰላም እንዲሰፍን በወሰዳቸው ርምጃዎች የፅንፈኛውና አሸባሪው ቡድን እኩይ አላማ በዘለቄታዊነት እየከሸፈ ነው። በወታደራዊ ሳይንስ በተቀመረው ሰልታዊ ውጊያ የጥፋት ቡድኖችን ህዋስ ለይቶ በመምታት ውጤታማ ስራ እያከናወነ የሚገኘው ሰራዊቱ ህገ-ወጥ የሰዎች፣ የገንዘብና የኮንትሮባንድ ዝውውርን በመቆጣጠር የእኩይ ቡድኖችን እስትንፋስ እየቆረጠም ይገኛል። በግዳጅ ቀጣና ህዝባዊ መድረኮች የሚነሱ ሀሳቦችን ወደ ውጤት በመቀየርም የልማትና የሰላም ተግባራትን አጠናክሮ እያስቀጠለ ነው። ኢትዮጵያዊ ወኔን በመላበስ ዘመኑ የደረሰበትን ትጥቅ፣ ዕውቀትና ክህሎት በመያዝ የታሪካዊ ጠላቶችን እኩይ አላማ እያመከነ በደም የተጻፈ ወርቃማ ገድሉን በከፍታ ሰንደቅ ሰቅሏል። የዚህ ባለ ደማቅ ታሪክ እና የአሸናፊነት ተምሳሌት የሆነ ሰራዊት አባል መሆን ደግሞ ድርብ ክብር ነው። የአሸናፊነት እና የጀግንነት ተምሳሌት የሆነው ሰራዊት ወኔ የተጋባባቸው የኢትዮጵያ ወጣቶችም ሰራዊቱን ለመቀላቀል ያሳዩት ተነሳሽነት ልብ የሚያሞቅ ነው። በሕብረ ብሔራዊት ኢትዮጵያ ጎጆ ከአራቱም አቅጣጫ የተሰበሰቡት የሰራዊቱ አባላት ህልማውቸና ጉዟቸው ወደ ሰላም፣ ልማትና ብልጽግና ነው። ለዚህ ደግሞ ከትውልድ ትውልድ ደም እየተቀረጸ የመጣው ኢትዮጵያዊ ጀግንነት ጉልበት ሆኖት የማይሻገረው ተራራ ድል የማይነሳው ግዳጅ የለም። ከራስ በፊት ለህዝብና ለሀገር በሚል እሴት የታነፀው ሠራዊቱ በህዝባዊ አመለካከትና ተግባሩ ሁሌም የሚመሠገን ዛሬም ለአህጉር እና አለም አቀፍ ተልእኮዎች ተመራጭ ሃይል ነው። የሀገር አለኝታ የሆነውን ሠራዊት በልዩ ልዩ መልኮች መደገፍ፣ አሳሳች መረጃዎችን መከላከል፣ በአለም አቀፍ መድረኮች የሰራዊቱን ገጽታ መገንባት ከአውደ ውጊያው እኩል መዘጋጀትና መዋጋት ያንተ፣ ያንቺ ፣የኔ፣ የኛ የሁላችንም ሃላፊነት ነው። ባለፈው ጥቅምት በተከበረው 116ኛው የሰራዊት ቀን ላይ የአገር መከላከያ ሰራዊትን ማክበር ኢትዮጵያን ማክበር ነው ሲሉ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድማርሻል ብርሃኑ ጁላ መግለጻቸውም ይሄንኑ ተልዕኮ ታሳቢ ስላደረገ ነበር። ሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝቦች ያሉበት ትንሿ ኢትዮጵያ መሆኑንና የአገር አደራ የተረከበ የኢትዮጵያ ሉዓላዊነት የመጨረሻ ምሽግ መሆኑን መግለጻቸውም አይዘነጋም። የጀግናው መከላከያ ሠራዊት አባላትም “ለኢትዮጵያ የአሸናፊነቷ ሚስጥሮች፤ የማንዝል ብርቱ ክንዶች ደጀን የህዝብ ልጆች” እኛ ነን እያሉ ዘላለማዊ ቃል ኪዳናቸውን በከፍታ ያውለበልባሉ።  
ታሪክ አስታዋሽ፣ በወንድማማችነት የተመሰረተና ትብብርን ያፀና ዲፕሎማሲያዊ ጉዞ
Jun 7, 2024 650
ክቡር ጠቅላይ ሚንስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በደቡብ ኮሪያ እና በሲንጋፖር የነበራቸው ቆይታ፣ ኢትዮጵያ ለጀመረችው የኢኮኖሚ ማሻሻያ፣ እድገት እና የለውጥ ጉዞ (ሪፎርም) ታላቅ አሻራ አኑሯል። በሁለቱ ሀገራት የተደረገው ጉዞ አዳዲስ ልምዶች ለመቅሰም፣ የኢንቨስትመንት አማራጮችን ለማስተዋወቅ፣ ከሀገሮቹ ጋር አዳዲስ የትብብር እና የግንኙነት ማዕቀፍ ለመፍጠር እንዲሁም እያደገ ላለው ኢኮኖሚያችን ቀጣይነት የፋይናንስ ድጋፍ ለማስፋት ጭምር ያለመ ሲሆን ይህንኑም በተጨባጭ አሳክቷል። ኮሪያና ሲንጋፖር ባለፉት ስልሳ እና ከዚያ በላይ ዓመታት እጅግ ዝቅተኛ ከሆነ የዕድገት ደረጃ ተነስተው አስደናቂ ማህበረ- ኢኮኖሚያዊ ዕድገት በማስመዝገብ ከዓለማችን የበለፀጉ ሀገራት ተርታ መሰለፍ የቻሉ ናቸው። ለተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ፣ ለሰብአዊ ሀብት ልማትና በኢኮኖሚያቸው ውስጥ የየሀገሮቻቸው መንግስታት የነበራቸው ወሳኝ ሚና፣ ለዕድገት እና ብልጽግናቸው ቀጣይነት የማይተካ ድርሻ አበርክቷል።   በዚህ ሂደት በየወቅቱ የነበሩ መሪዎቻቸው ባሳዩት ቁርጠኝነት እና በተከተሉት የኢኮኖሚ ፖሊስ ሀገራቱ የሚመሳሰሉ በመሆኑ ኢትዮጵያ ለጀመረችው የብልጽግና ጉዞ ጠቃሚ ልምድ የሚቀሰምባቸው ናቸው። ይሁን እንጂ ሁለቱም ሀገራት ለዕድገት ዘርፎች በሰጡት ትኩረት እና ቅደም ተከተል ባለቸው ተነፃፃሪ ጠቀሜታ ወይም comparative advantage እና ጂኦግራፊያው ሁኔታ የሚለያዩ ናቸው። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ከሀገራቱ መሪዎች ጋር ያደረጉዋቸው ውይይቶች፣ የተመረጡ የመስክ ምልከታዎች እና የተደረጉ የትብብር ማዕቀፎች ብሎም ኢትዮጵያ ለውጭ ባለሃብቶች እየከፈተች ያለው አዳዲስ የኢንቨስትመንትና የገበያ ዕድሎችን የማስተዋወቅ ጉዳይ እነዚህኑ ሁኔታዎች ታሳቢ ያደረጉ ናቸው። በውይይት የዳበሩት እነዚሁ የትብብር ማዕቀፍ ስልቶችም ሀገራችን ከነደፈቻቻው ፖሊሲዎች እና የእድገት አቅጣጫዎች ጋር እንዲጣጣሙ ጥረት የተደረገባቸው ናቸው።ከዚህ አኳያ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶ/ር) እና የልዑክ ቡድናቸው በሁለቱም ሀገሮች የነበረቸው ቆይታ ፍሬያማ እና የተሳካ ነበር።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኮሪያ ያደረጉት ጉብኝት ታሪክን ከማስታወስ የጀመረ ነው። ኢትዮጵያ በ1950ዎቹ የኮሪያ ጦርነት በሰላም ማስከበር ተልዕኮ ተሰማርታ ለኮሪያ ሰላም መስዋዕትነት የከፈሉ የቃኘው ሻለቃ ጦር አባላትን በማስታወስ፣ የሁለቱ ሀገራት ህዝቦች ግንኙነት በደም የተሳሰረ መሆኑን ባመላከተ አግባብ በቹንችዮን፣ የኮሪያ ጦርነት የመታሰቢያ ስፍራ የአበባ ጉንጉን አስቀምጠዋል። ይህም ኢትዮጵያ በዓለም የሰላም ማስከበር ታሪክ ቀዳሚ ሚና እንዳላትና ለሰላም ያላት ዋጋ ሁልጊዜም የማይለዋወጥ መሆኑ የተገለፀበት፣ የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ከ60 ዓመት በላይ ያስቆጠረና የሀገራቱ የመጪው ጊዜ ግንኙነት የበለጠ ጠንካራ እና ዘርፈ ብዙ ሆኖ እንደሚቀጥል የተመላከተበት ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ፣ በኮሪያ ሪፐብሊክ ከሀገሪቱ መሪ ጋር በነበራቸው ቆይታ ሁለቱን ሀገራት ተጠቃሚ በሚያደርጉ የኢኮኖሚ ትብብር ማዕቀፎች ላይ ስምምነት ተደርሷል። የመግባቢያ ስምምነትም ተፈርሟል። ኢትዮጵያን ለአራት ተከታታይ ዓመታት ተጠቃሚ የሚያደርግ የፋይናንስ ድጋፍም ተገኝቷል። በኮሪያ መንግስት ድጋፍ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እየተከናወነ የሚገኘው የወንዝ ዳርቻ ልማት ይበልጥ በሚጠናከርበት ሁኔታም ላይ ስምምነት ተደርሷል። የኮሪያ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ባሉ የኢንቨስትመንት ዕድሎች በተለይም በግብርና፣ በማዕድንና በአምራች ኢንደስትሪ ዘርፎች በሚሳተፉበት ሁኔታ ላይ ምክክር ተደርጓል። ከውይይቶቹም ጎን ለጎን ሀገራችን ለጀመረችው ፈጣንና አመርቂ የልማት ስራዎች ልምድ መቅሰም የሚያስችሉ የመስክ ምልከታዎች ተካሂዷል ። የልዑካን ቡድናቸውም የመሪዎቹን ስምምነቶችና ውይይቶች ታሳቢ ያደረጉ እና ይበልጥ የሚያፀኑ ውይይቶችን ከአቻ ተቋማት መሪዎች ጋር አካሂደዋል።   በኮሪያ የተሳካ ጉብኝታቸውን አጠናቀው ወደ ሲንጋፖር ያመሩት ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አሕመድ፣ በሲንጋፖር በነበራቸው ቆይታ ከሀገሪቱ ፕሬዚዳንት እና ጠቅላይ ሚንስትር ጋር በሁለትዮሽ ግንኙነት ጉዳይ ተወያይተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመራው ልዑክም የኢትዮጵያ መሪ ወደ ሲንጋፖር ከተጓዘ ከ68 ዓመታት በኋላ የተጓዘ የመጀመሪያው ልዑክ ሆኗል። የሲንጋፖርና የኢትዮጵያ ይፋዊ ያልሆነ ግንኙነት የሚጀምረው የሲንጋፖር መስራች አባት የሚባሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ሊ ኩዋን ዩ በፈረንጆቹ 1964 ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት ነው፤ የጉብኝታቸው ምክንያትም ሲንጋፖር በቅኝ ግዛት ስለነበረች ነጻነቷን ለማግኘት የአፍሪካ ሀገራትን ለማግባባት ነበር። በዚያው ዓመት በርካታ የአፍሪካ ሀገራት ነጻነታቸውን ለመቀዳጀት ጫፍ ላይ የነበሩበት በመሆኑና ተመሳሳይ የጸረ ቅኝ ግዛት ትግል አቋም በመኖሩ ለሲንጋፖር አፍሪካ ተመራጭ አህጉር ነበር። ከዚህ አኳያ ኢትዮጵያ ከኮሪያም ሆነ ከሲንጋፖር ጋር ያላት ታሪካዊ ግንኙነት አሁን ያልጀመረና የጠበቀ ትስስር እንዳለው ያመለክታል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በሲንጋፖር ከሀገሪቱ መሪዎች ጋር የነበራቸው ውይይት አንዱ ትኩረት አረንጓዴ ልማት ሲሆን በትምህርት፣ በቀልጣፋ የህዝብ አገልግሎት እንዲሁም በከተማ ልማት ስራዎች ዙሪያ ሀሳቦችን ተለዋውጠዋል። በኢትዮጵያ እና በቀጠናው ስላለው የሰላም ሁኔታ፣ የኢንቨስትመንት አማራጮች እና ዕድሎች እንዲሁም በቴክኖሎጂ፣ በሎጀስቲክ እና ትራንስፖርት፣ በቱሪዝም ዘርፎች ፣ እንዲሁም በቀጣይ የትብብር መስኮች ላይ ሰፋ ያለ ውይይት አካሂደዋል።   የሁለትዮሽ ግንኙነትን የሚያጠናክር የስምምነት ማዕቀፍም ተፈርሟል። ሲንጋፖር በአገልግሎት ዘርፍ፣ በቴክኖሎጂ፣ በቱሪዝም እና በሎጂስቲክ ሀብ የላቀ ደረጃ ላይ የደረሰች ሀገር በመሆኗ ኢትዮጵያ ለጀመረችው የአራንጓዴ አሻራ፣ የቱሪዝም መሠረተ ልማት ግንባታ እና የኮሪደር ልማት ሰፊ ልምድ የሚቀሰምባት ናት። ይህ እንዳለ ሆኖ ጉብኝቱ ሲንጋፖር ተመራጭነቷን በአረንጓዴ ልማት ጭምር እንዴት እያሳካች እንደሆነ ትምህርት የተወሰደበትና ኢትዮጵያ የጀመረችው የአረንጓዴ ልማት ስራዎች በትክክለኛ ደረጃ እየተጓዙ ስለመሆኑ ግንዛቤ የተገኘበት፣ ይህንኑ ታሳቢ ያደረጉም የተመረጡ የመስክ ምልከታዎች የተካሄዱበት ነው። በሀገሪቱ ቁልፍ ለሆኑና እና ለተመረጡ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ስላለው የኢንቬስትመንት አማራጮች፣ የፖሊሲ ማሻሻያዎችና ተያያዥ ጉዳዮች በልዑኩ ገለጻ ተደርጎላቸዋል። ባለሀብቶቹ ላነሱት ጥያቄዎችም አጥጋቢ ምላሽ ተሰጥቶአቸዋል። ባለሀብቶቹም በተለይም በቴክኖሎጂ፣ በሎጅስቲክስ እና ደረቅ ወደብ ግንባታ እና አስተዳደር ፣ በግብርና ልማት እና አገልግሎት መስኮች ለመሰማራት ፍላጎት እንዳላቸው ገልፅዋል። ከዚህ አኳያ ሲታይ ክቡር ጠቅላይ ሚንስትሩ እና የልዑክ ቡድናቸው በሁለቱም ሀገሮች የነበረቸው ቆይታ ፍሬያማ እና የተሳካ፣ የኢትዮጵያ ተፈላጊነትና አስፈላጊነት የታየበት ነበር። በሁለቱም ሀገሮች ለክቡር ጠቅላይ ሚንስትሩ እና ልዑካቸው ወንድማዊ እና ፍቅር የተሞላበት ደማቅ አቀባበል ተደርጓል። በዚህ አጋጣሚ የሁለቱንም ሀገር መንግስት እና ህዝብ ከልብ እናመሰግናለን!! የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ለገሰ ቱሉ (ዶ/ር)
በአንድነት የመምከር ብሩህ ተስፋ! 
May 13, 2024 794
በአንድነት የመምከር ብሩህ ተስፋ! በቀደሰ ተክሌ (ከሚዛን አማን) ሀሳብ ያፋቅራል፤ ሀሳብ ያቃርናል። በማንኛውም ጊዜ የሚነሳ ሀሳብ በውይይት ዳብሮ በሰዎች የሕይወት ኡደት ውስጥ መግባባት፣ መተማመን እና መስማማት የሚሉ መሠረታውያንን ሲያስከትል ሰዎችን ልብ ለልብ በማገናኘት አንድ የማድረግ ኃይሉ ከፍያለ ይሆናል። ያን ጊዜ ሰላምና ፍቅር በአብሮነት ታጅቦ በጋራ ማንነት ይደምቃል። በተቃራኒው ሀሳብ በልዩነት የተወጠረ ከሆነ በጊዜ ሂደት እየከረረ ወዳጅነትን የመበጠስ አቅም ያገኛል። ይህ እንዳይሆን ሀሳቦችን በውይይት ማቀራረብ የመጀመሪያ ጉዳይ የመጨረሻም መፍትሄ ነው። ሰው እንደመልኩ አስተሳሰቡና ግንዛቤው ቢለያይም ዙሮ አንድ የሚሆንበት ሰብዓዊ ፀጋ ተችሮታል። ይህም ከራስ በተጨማሪ የሌሎችንም ሀሳብ አዳምጦ የጋራ መግባባት ላይ መድረስ የሚያስችል ማስተዋል ነው። ማስተዋል ደግሞ ግራ ቀኝን የመቃኘትና የመመዘን ጥበብ ሲሆን፤ የሌሎችን ሀሳብ ከእውነታ ጋር ለማጤን ይረዳል። መነጋገር በብዝኃ አስተሳሰብ እና ማንነት ውስጥ የመከባበር እሴትን በማጉላት በሕዝቦች መካከል አንድነትንና መቀራረብን ይፈጥራል። ፍቅር ሰብኮ፣ ሰላም ዘርቶ አብሮነትን ለማጨድ የሚያስችል ከጥንትም በማህበረሰቡ ወስጥ ያለው ጥበብ ውይይት ነው። ማህፀነ ለምለሟ ኢትዮጵያ የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦችን ከብዝሃ ባህልና እምነት ጋር አቅፋ ይዛለች። ብዝኃነት ውስጥ ያለው ኢትዮጵያዊነት ስሟን በአብሮነት የመኖር ተምሳሌት የሚያስጠራ ነው። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በሚያዘጋጀው ምቹ ሁኔታ ኢትዮጵያዊያን በችግሮቻቸው ላይ በጋራ ሊመክሩ ነው። በምክክሩም "የኢትዮጵያዊነት ቀለም፣ የአብሮነት መንፈስ፣ የመከባበር እና የሰላም እሴት አብቦ ፍሬው በምድሪቱ እንዲታይ ያደርጋል" የሚል ብሩህ ተስፋን ሰንቀዋል። ለችግሮቻቸው መፍቻ ቁልፍ ውይይት መሆኑን ስለተረዱትም ምክክሩን አጥብቀው ሽተዋል። በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ የሰላምና ደህንነት መምህር እንዳለ ንጉሴ እንደሚሉት፤ በአብዛኛው የአፍሪካ ሀገራት ችግሮች ሲፈጠሩ ለመፍትሄው አፈ ሙዝ እንጂ ጠረጴዛ አይታሰብም። ለችግሮች መፍትሄ በሀይል ይገኝ ይመስል ከሰላማዊ ውይይት ይልቅ ጉልበትን መርጠው ተመሳሳይ አዙሪት ውስጥ የገቡ አገራት ጥቂት አይደሉም። በዚህም ወደ መፍረስ አልያም ወደ መዳከምና አቅም አልባ የመሆን ደረጃ ላይ የደረሱ አገራት አሉ። ኢትዮጵያ ግን ከዚህ በመሻገር የውይይት ዐውድ በማዘጋጀት ልጆቿ በችግሮቻቸው ላይ በአንድነት እንዲመክሩ ተግታ እየሠራች ነው። ኢትዮጵያዊያንም በአንድነት ተወያይተው ከልዩነቶቻቸው ይልቅ አንድ የሚያደርጓቸውን አጉልተው ለማውጣት ጫፍ ላይ ደርሰዋል። ሀገራዊ ምክክሩ ደግሞ በአንድ ሀገር ውስጥ ችግሮችን ከመፍታት ባለፈ በመንግስትና በሕዝብ መካከል መተማመንና ግልጽነትን ለመፍጠር ትልቅ አቅም እንዳለው ነው መምህር ንጉሴ የገለጹት። እንደመምህሩ ገለጻ፤ ከውይይቱ እንደ ሀገር ፖሊሲ ሊቀረጽባቸው በሚገባቸው ጉዳዮች ላይ መረጃዎችን በገብዓትነት ለመሰብሰብ ይቻላል። በምክክሩ በዋናነት የሰላምም ሆነ የግጭትን ውጤት የሚቀምሰውን ማኅበረሰብ ማሳተፍ ችግሮችን በጋራ የመፍታት ልምድ እንዲዳብር ያደርጋል። ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በዚህ ረገድ አካታች መርህን መከተሉ በዜጎች ውስጥ ጥሩ ተስፋ እንዲፈጠር አድርጓል። የሕዝብን ፍላጎት አዳምጦ ምላሽ የሚሰጥ አካልን ፊት ለፊት አስቀምጦ ምክክር መደረጉ ከውይይት ማግስት አዎንታዊ ምላሽ ለማግኘት ያስችላል። በሁሉም ዘንድ ተቀባይነቱ ከፍ ያለ መንግስት የመፍጠር ዕድልን ከማስፋት ባለፈ ልዩነትን የሚያሰፉ ችግሮችን ከስር መሠረቱ የመንቀል አጋጣሚን እንደሚያመጣ ነው መምህር ንጉሴ የገለጹት። የምክክር ኮሚሽኑ ዜጎችን አንድ የሚያደርጉ ጉዳዮችን በማንጸባረቅ የጋራ እሴት የመገንባት ኃላፊነት ተጥሎበታል። ይህ እውን በሚሆነበት ጊዜ የእኔነት ስሜት ተመናምኖ የእኛነት የሚለመልምበት አስተሳሰብ በዜጎች ውስጥ ይሰርጻል ተብሎም ይጠበቃል። ኢትዮጵያ የሚያስፈልጋት ዘላቂ ሰላም፣ አብሮነትና በጋራ ሀገር በአንድነት ተባብሮ መስራትና በፍቅር የመኖር እሴት እንዲለመልም ምክክሩ መሠረት ይጥላል። የኢትዮጵያውያን እሴትና የኮሚሽኑ ቅቡልነት! ኢትዮጵያውያን የሀሳብ ልዩነቶችን በምክክር መፍታት የሚያስችል ባህላዊ እሴት ያላቸው ሕዝቦች ናቸው። ምንም እንኳ ከቦታ ቦታ ቢለያይም እያንዳንዱ ብሔረሰብ ግጭት የሚያስወግድበት ባህላዊ ሥነ ሥርዓት አለው። የአፈጻጸሙ ሂደት ጉራማይሌ ሊሆን ቢችልም እንኳ የሰላም ግንባታ ሂደት መሠረቱ ውይይት ነው። ይሁንና ችግሮችን በውይይት የመፍታት ልምዳችን በዘመናት ሽግግር ውስጥ የመደብዘዝ ዕድል ገጥሞታል። ይሁንና ከማኅበረሰቡ ማንነት ውስጥ ጨርሶ ስላልጠፋ ይህ በጎ እሴት አሁን እየታየ ላለው የሰላም እጦት ሁነኛና አስተማማኝ መፍትሄ ስለሚያመጣ ምክክሩ ተቀባይነት አግኝቶ በተስፋ ሊጠበቅ ችሏል። በሌላ በኩል የምክክር ኮሚሽኑ የሚፈጥረው ምቹ ሁኔታ ዜጎች ችግሮቻቸውን ተናግረው ሊደመጡ የሚችሉበት ሰፊ መድረክ በመሆኑ ከሕዝቡ ዘንድ አዎንታዊ ምላሽ አግኝቷል። መምህር እንዳለ እንደሚሉት፤ ውይይት ለሰላም ግንባታ ብቸኛ አማራጭ ሲሆን፤ መንግስትም የሕዝብን ሀሳብ ለመስማት ዕድል ያገኛል። በእዚህም የምክክር ኮሚሽኑ ተቀባይነት መጉላቱን ነው የገለጹት። ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ኢትዮጵያውያን በችግሮቻቸው ላይ መክረው ለመግባባት የሚያስችላቸው ነው። የውይይት መድረኩ አንዱ የሌላውን ችግር በመረዳት ሀገራዊ እይታውን የሚያሰፋበት መነጽር ይፈጥርለታል። ለመፍትሄ ከመነሳት በፊት ችግሮችን ማወቅ ይቀድማልና በምክክር ወቅት ኢትዮጵያ ምን መልክ እንዳላት ዋና ዋና ችግሮቿስ ምንድን ናቸው? የሚሉት በተወያዮች በኩል ይንጸባረቃሉ። የተወያዮች ኃላፊነት የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ሥራ ውጤታማነት በተወያዮች የሚወሰን ነው። ሁሉም ኢትዮጵያውያን በተለያዩ አደረጃጅቶች ሀሳቦቻችንን ያደርሱልናል ብለው የወከሏቸው ግለሰቦች አሉ። በመሆኑም እነዚህ የህብረተሰብ ተወካዮች ላለመግባባት ምክንያት የሆኑ ዋና ዋና ችግሮችን ለውይይት ይዞ ለመቅረብ ተገቢውን ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ይህን ሀሳብ የሚያንጸባርቁት በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሰቲ የታሪክ እና ቅርስ አስተዳደር ትምህርት ክፍል መምህር አጥናፉ ምትኩ ከማህበረሰብ ተወካዮች በሳል ሀሳብ ይዞ መቅረብ እንደሚጠበቅ ይገልጻሉ። የግል ሀሳብን ሳይሆን የወከሏቸውን ህዝቦች ፍላጎትና አስተሳሰብ ማንጸባረቅ የተወያዮች ግዴታ ነው። በውይይት ወቅትም የራስን ብቻ ሳይሆን የሌሎችንም ሀሳብ የማድመጥ ባህልን አጉልቶ ማንጸባረቅ ይጠበቃል። በሌላ በኩል ተወያዮች ሀሳብ ከማመንጨት ጀምሮ የጋራ መፍትሄ የማፍለቅ ሃላፊነትም አለባቸው። የመቻቻል እና የመከባበር ልምድ በውይይት ወቅት ጎልቶ እንዲወጣ ከማድረግ ባለፈ ወደ ማኅበረሰቡ ማዛመትም አስፈላጊ ነው። ያለፈውን በማንሳትና በመቆስቆስ አንዱ ሌላውን የሚከስ ሳይሆን ቁስሉን ለማከም መፍትሄ የሚፈልግ ስብዕናን መላበስ ያስፈልጋል። በእዚህ መንፈስ ለውይይት ከቀረብን ለዘመናት ሳያግባቡን የቆዩ ችግሮችን ፈትቶ እንደ ሀገር ለመሻገር አቅም መፍጠር ይቻላል። የዜጎች ድርሻ ተስፋ የነገ ብርሃን ጮራ ነው፤ ነገን የመመልከት መነጽር። ተስፋ ስኬታማ የሚሆነው ደግሞ ዛሬ በሚሠራው ሥራ ነው። እንጀራ ተጋግሮ ከመበላቱ በፊት ጤፍ ተፈጭቶ መቦካት አለበት። እንጀራ የመብላት ተስፋ ጤፍ ከመዝራት ጀምሮ የማስፈጨትና የማቡካት ሂደትን ይጠይቃል። የምክክር ኮሚሽን ፍሬያማ ውጤት በቅድመ ዝግጅት ምዕራፉ የጠራ ግንዛቤ መያዝና ቀና አመለካከት መላበስን ይጠይቃል። ይሆናል፤ ይሳካል ብሎ አዎንታዊ እንቅስቃሴ ማድረግና ከአላስፈላጊ ትችት መራቅም እንዲሁ። መምህር አጥናፉ እንዳሉት የምክክር ኮሚሽኑ ዓላማ ግቡን እንዲመታ በተለይ የአገር ሽማግሌዎች አገር በቀል እውቀቶችን በማቀበል፤ ምሁራን የሌሎች ሀገራትን ተሞክሮ በመቀመር እና የምርምር ሥራዎችን በማቅረብ የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል። አካታችነቱን ተጠቅመው ሀሳብ ለማዋጣትና ለመደገፍ ለዜጎች የተሰጠ እድል በመሆኑ በአገባቡ በመጠቀም ተባብሮ እውን ማድረግ ይገባል። ኢትዮጵያ ብሩህ የአብሮነትና የሰላም ተስፋን በምክክር ኮሚሽኑ ላይ የመጣሏ ምሥጢር የቤት ገበናን በቤት ውስጥ መፍታት የሚችል ቁልፍ ይዞ ስለተነሳ ነው። ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ሀገር በቀል እውቀቶችን ተንተርሶ ከባዳ ዐይንና ጆሮ የራቀ ሁነኛ መፍትሄን እንካችሁ እያለ ነው። ዜጎችም ለመቀበል እጃቸውን ዘርግተው በመጠባበቅ ላይ ናቸው። ይሄን ደግሞ በየአካባቢው ለኮሚሽኑ እየተደረገ ያለው የህዝብ አቀባበልና ድጋፍ ያረጋግጣል። ኮሚሽኑ አሁን የቀረውን የቅድመ ውይይት ሂደት ጨርሶ ወደዋናው ምክክር ሲገባ ከአንደበት ይልቅ ለጆሮ ቦታ ሰጥቶ በሰከነ መንፈስ ውይይቱን የማስኬድ ኃላፊነት መሸከም ከሁሉም ይጠበቃል። ሰላም !!!
ከፈተናዎች ባሻገር . . . !
May 4, 2024 927
ከፈተናዎች ባሻገር . . . ! (በቀደሰ ተክሌ ከሚዛን አማን ኢዜአ) በዓለም ውስጥ ሆኖ በአንዳች ምክንያት የወደቀ ይነሳል፤ የታመመ ይድናል፤ የፈረሰ ይጠገናል፤ የደከመ ይበረታል፤ የተኛ ወይም ያንቀላፋም ይነቃል። ይህን እውነት ሰው በልቡ ተስፋ አድርጎ ውሎ ያድራል።ነገን ያልማል። "ሲጨልም ይነጋል" እያለ ለራሱ ይጽናናል። መከራ ሲበዛበት "ሊነጋ ሲል ይጨልማል" በሚል አዲስ ተስፋን በውስጡ ይዘራል። ከእነዚህ ተቃራኒ የሰው ልጅ ከህይወት ዑደት ኩነቶች ባሻገር በተለያዩ የእምነት ተቋማት አስተምህሮ ደግሞ የሞተ የሚነሳበት መንፈሳዊ ተስፋ አለ። ይህም ትንሣኤ ይባላል- ከሞት በኋላ የሚኖር ሕይወትን የሚያሳይም መነጽር። "ትንሣኤ" ማለት የግዕዝ ቃል ሲሆን፤ ቀጥተኛ ትርጉሙ መነሳት ነው። መነሳት የሚነገረው ለወደቀ፤ ለደከመ እና ለሞተ ነው። እንዲሁም ከነበረበት ከፍ ማለት ቀና ማለት መለወጥና ወደ አዲስ መልካም ነገር መሸጋገርን ያመለክታል። በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ ትንሣኤ የሚከበረው የኢየሱስ ክርስቶስን ከሞት መነሳትን መሠረት በማድረግ ነው። ክርስቶስ በምድር ሲመላለስ የሰው ልጆች ማድረግ ስለሚገባቸው በጎ ምግባራት እርሱ በመተግበር አስተምሯል። የበጎ ተግባራት ውጤት ደግሞ ከሞት በላይ ራስን ከፍ አድርጎ በሕይወት ዙፋን ላይ መቀመጥ እንደሆነ አሳይቷል። ፍቅር እንዲጎለብት ለሌላው መኖርና አልፎም መስዋዕት መሆንን በግልጽ አንጸባርቋል። እርሱ መልካም ነገር አድርጎ "እናንተ እንዲሁ አድርጉ" ብሏል። ለአብነትም ፍቅር በቀዳሚነት የሚጠቀስ ትምህርቱ ነው "እርስ በእርስ ትዋደዱ ዘንድ ትዕዛዜ ይህች ናት" ብሏል። ፍቅሩን ለሰው ልጆች ራሱን አሳልፎ በመስጠት ገልጧል። ነገ ምን እንዲያውም ከደቂቃዎችና ሰዓታት በኋላ ምን እንደሚፈጠር በማናውቀው ተገድቦና ተተምኖ በተሰጠን የህይወት ዑደት ውስጥ በምናልፋቸው የትኞቹም ጎዳናዎች ምህረትን፣ ይቅር ባይነትን ይጠየቃል። ለሰው ልጅ ለራሱም ቢሆን ቂምና ቁርሾ ያላደረበት ልብ ያስፈልገዋል። የወደደንን ወይም የሰበሰበንን ሳይሆን ተቃራኒውን የፈጸመብንን የመውደድና ፍቅርን በተግባር የማሳየት ልምምድ እንዲኖረን ያስተምራል። ይህም ከራሳችን ጀምሮ ለአካባቢያችን ሁሉ ሰላምና መረጋጋትን ይፈጥራል። ሌላው የተግባር ትምህርቱ ትህትና ነው። የሰው ልጆችን ለማክበር ራሱን ዝቅ አድርጓል። የደቀ መዛሙራቱን እግር ተንበርክኮ አጥቧል። "እናንተም እንዲሁ ለሌሎች አድርጉ" ሲልም አስተምሯል። የዚህ ዓይነቱ ተግባር ዛሬም በኢትዮጵያውያን እሴት ውስጥ ይስተዋላል። በትውፊት ከትውልድ ወደ ትውልድ በመተላለፉ መጥቷል። ቤታችን የወላጆቻችንን አልፎም የመጣን እንግዳ እግር ማጠብ የመልካም ሥነ ምግባር ምገለጫችን ሆኖ ቆይቷል። ይህ እርስ በርስ መከባበር እያጠነከረ ይመጣል፤ ውሎ ሲያድርም በስነ ምግባር የታነጸ የጠንካራ ማህበረሰብ መገለጫም ይሆናል። ትህትና ከአንገትን ጎንበስ ብሎ ሰላምታ መሰጣጣት ብቻ አይደለም። ሌሎች የተሻሉ እንዲሆኑ ማሰብን ያካተተ ከልብ የሚፈልቅ ተግባር ነው። በትዕቢት አውቃለሁ ባይነት ሳይሆን ራስን ዝቅ በማድረገ መንፈስ የተገዛ ማንነት ማዳበርን ይጠይቃል። ድርጊት የሀሳብ ውጤት ነው። ስለሆነም እርስ በርሳችን ከቤተሰብ እስከ ማህበረሰብ እንዲሁም በስራ ቦታችን ካሉ ባልደረቦቻችንን ከልብ በመነጨ ትህትና መቀበልና ማስተናገድ አልፎም መታዘዝ ይጠበቅብናል። ይህ ነው የትህትና ጥቅ እሴቱ። በጎነት፣ ፍቅር፣ ትህትና፣ ለጋስነትና ቅንነትን የሰው ልጅ ገንዘቡ ቢያደርግ ሞትን አሸንፎ ይከብራል። ከመውደቅ ባሻገር መነሳት አለ። ከጨለማ በኋላ ብርሃን ይኖራል። ይህም ከጽልመትና ከአስቸጋሪ ነገሮች አልፈን ብርሃን ማየት እንደሚቻል የጸና ተስፋ በመያዝ ነጋችንን ማየት ይኖርብናል። ትንሣኤ ደስታ ነው፥ ከድቅ ድቅ ጨለማ በኋላ የሚገኝ ልዩ ብርሃን፤ ከመቃብር በላይ የሚገኝ ሐሴት ነው። የትላንት መከራ ላይ የታነጸ ጽኑዕ ደስታ፤ የትላንት መልካም ነገርን መነሻ አድርጎ የሚገኝ ክብር ነው። የሰው ልጅ በፈተናዎች ውስጥ ሆኖ ነገን ተስፋ አድርጎ ጠንክሮ መስራት ከቻለ መልካም ነገር ሁሉ ማግኘት ይችላል። ዛሬም ዓለም ብዙ ውጣ ውረዶችን ታስተናግዳለች። እንደ አገር ኢትዮጵያ ብዙ ችግሮች እያጋጠሟት ነው። ችግሮቹና መከራው ማብዛቱ የነገን ትንሣኤ ለማምጣት ነው። ከፈተናዎች ባሻገር ድል አለ፤ ትንሣኤ ይገለጻል። ለዚህም ነው ምንም ፈታኝ ነገር ቢኖር፣ ችግሮች ቢደራረቡም ተግቶ ሰርቶ ወደ ብርሃኑ መውጣት ይቻላል የምን ለው። የትንሣኤ በዓል ከበዓል ባሻገር በበጎ እይታ በመቃኘት፣ በፍቅር በመታነጽና የቅንነት ጎዳናን በመያዝ ለአገር እና ለራሳችን ክብርን ለመጎናጸፍ ተግባራዊ ምላሽ በመስጠት መሆን አለበት።      
በድላችን ሐውልት ክላሽንኮቭ መሳሪያ ይዘው ሐውልት የተቀረጸላቸው የካራማራው ዘማች አቶ በቀለ ገመቹ 
Mar 5, 2024 4258
አቶ በቀለ ገመቹ ወይም በቅፅል ስማቸው አሚኮ ይባላሉ፤ በሙያቸው ኤሌክትሪሺያን ናቸው። በ1969 ዓ.ም በዚያድባሬ የሚመራው የሶማሊያ አገዛዝ ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት ሀገር ስትደፈር ቁጭት ተሰምቷቸው ወደ ጦር ሜዳ መዝመታቸውን ይናገራሉ። ጦር ሜዳ ከመዝመታቸው ባሻገር የኤሌክትሪክ ባለሙያ በመሆናቸው "በራ በራ የድል ጮራ" የተሰኘውን ዓርማ በመቅረጽ በ14ቱ ክፍላተ ሀገር እንዲበራ ማድረጋቸውንም ያነሳሉ። በዚህም ከወቅቱ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ኮሎኔል መንግስቱ ኃይለማርያም እና ከኩባው ፕሬዝዳንት ፊደል ካስትሮ መሸለማችውን ያወሳሉ። ታንክ ማራኪው አሊ በርኬ ጓደኛቸው እንደሆኑ የሚናገሩት አቶ በቀለ፤ በተለያዩ ዐውደ ግንባሮች መሳተፋቸውን አስታውሰዋል። አቶ በቀለ ጥቁር አንበሳ በሚገኘው የኢትዮ-ኩባ ወዳጅነት ፓርክ በሚገኘው የድላችን ሐውልት ላይ ክላሽንኮቭ መሳሪያ ይዘው ሐውልት ተቀርጾላቸዋል። ሐውልት እንዲቀረጽ የተደረገበት ፎቶግራፍ በያኔው ሶስተኛው አንበሳው ክፍለ ጦር በኋለኛው ምሰራቅ ዕዝ በር ላይ በቀኝ እጃቸው መሳሪያ ከፍ አድርገው ይዘው የተነሱት ፎቶ ግራፍ እንደሆነ ገልጸው፤ በዚህም ደስተኛ እንደሆኑ ይናገራሉ። ከእርሳቸው ጎንም መንበረ የምትባል ሌላ ኢትዮጵያዊ ዘማችና መትረጊስ ተኳሽ ሴት ባደረገችው አስተዋፅኦና በደረሰባት አካል ጉዳት ሐውልት እንደተቀረጸላት ያነሳሉ። የካራማራ ድል ታላቅ ድል ነው የሚሉት አቶ በቀለ ገመቹ፣ በርካታ ኢትዮጵያውያን መስዋዕትነት ከፍለውበት የተገኘና ሀገርን ያስከበረ መሆኑንም ይገልጻሉ። የካራማራ ዘማቹ አቶ በቀለ ገመቹ አሁናዊ ኑሯቸው ችግር ላይ እንደሚገኙና ድጋፍ እንደሚሹም ተናግረዋል። ሶማሊያን ለ21 ዓመታት ያስተዳደሩት ዚያድባሬ 'ታላቋን የሶማሊያ ሪፐብሊክ ለመመስረት' በሚል "ድንበራችን እስከ አዋሽ ይደርሳል" እያሉ በመዛት የጦርነት ነጋሪት መጎሰማቸው የሚታወስ ነው። ይሄን እውን ለማድረግ በ1969 በኢትዮጵያ ላይ ግልጽ ወረራ ፈጸሙ። የካቲት 26 ቀን 1970 ዓ.ም የኢትዮጵያ ጦር የእብሪተኛውን የዚያድባሬ ጦር ካራ ማራ ላይ ድል አደረገ፤ የኢትዮጵያ አሸናፊነትም በአደባባይ ታወጀ። ድሉ በየዓመቱ የካቲት 26 ቀን የሚታሰብ ሲሆን ዘንድሮም 46ኛ ዓመቱ ላይ ደርሷል።    
የአፍሪካ ዋንጫን በመሀል ዳኝነት  የመራችው ብቸኛዋ ሴት ዳኛ
Jan 28, 2024 3910
  በይስሐቅ ቀለመወርቅ እንደ መነሻ፡- በእግር ኳስ ውድድሮች የመሃል ዳኝነቱን ቦታ በብዛት የሚይዙት ወንዶች ሲሆኑ፤ አሁን ላይ አልፎ አልፎ ሴቶች ትልልቅ የእግር ኳስ ጨዋታዎችን ሲዳኙ አስተውለናል። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2022 በኳታር አስተናጋጅነት በተከናወነው 22ኛው የፊፋ የዓለም ዋንጫ፤ ፈረንሳዊቷ ስቴፋኒ ፍራፓርት፤ ኮስታሪካ እና ጀርመን ያደረጉትን ጨዋታ በመሀል ዳኛነት መርታለች። በዚህም በወንዶች ዓለም ዋንጫ ታሪክ በመሀል ዳኝነት የእግር ኳስ ጨዋታን የመራች የመጀመሪያዋ ሴት በመሆን ታሪክ ሰርታለች ። ዘንድሮ ደግሞ በኮትዲቯር አስተናጋጅነት እየተከናወነ በሚገኘው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ሞሮኳዊቷ ቦችራ ካርቡቢ፤ ውድድሩን እንዲመሩ ከተመረጡት 32 የመሀል ዳኞች መካከል ብቸኛዋ ሴት ናት። በዚህም በውድድሩ በጊኒ ቢሳውና በናይጄሪያ መካከል የተከናወነውን ሦስተኛ የምድብ ጨዋታ፤ በመሀል ዳኝት በመምራት፤ ታሪክ ጽፋለች። የሞሮኮ ዓለም አቀፍ ማኅበር የእግር ኳስ ዳኛ የሆነችው ቦችራ ካርቡቢ፤ በወንዶችም ሆነ በሴቶች አህጉራዊ የእግር ኳስ ውድድሮች ላይ በርካታ የመጨረሻ ምዕራፍ የእግር ኳስ ጨዋታዎችን ዳኝታለች። 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫን ብቸኛ የሴት ዳኛ ሆና የመራችው ቦችራ ካርቡቢ ማናት? ቦችራ ካርቡቢ በሞሮኮ ሰሜናዊ ክፍል በምትገኘው "ታዛ" ከተማ፤ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1987 ተወለደች። የዘር ግንዷ በሰሜን ምሥራቅ ሞሮኮ ከሚገኙት ሪፊያን ከሚባሉት የበርበር ጎሳ ዝርያ ካላቸው ሕዝቦች የሚመዘዝ ሲሆን፤ ለቤተሰቦቿ አምስተኛና የመጨረሻ ልጅ ነች። ገና በልጅነቷ ለእግር ኳስ ፍቅር ያደረባት ቦችራ ካርቡቢ፤ ኳስ መጫወት የጀመረችው በአንድ ትንሽ የወጣቶች ቡድን ውስጥ ነበር። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2001 በተወለደችበት ከተማ "ታዛ"፤ ለወንዶችና ለሴቶች የእግር ኳስ ዳኝነት ሥልጠና የሚሰጥበት ትምህርት ቤት ተከፈተ ። ይኼ ትምህርት ቤት ቀልቧን የሳበው ቦችራ፤ ሥልጠናውን መውሰድ ጀመረች። "እግር ኳስን እወዳለሁ፤ ራሴንም ላስተምር ፈለኩ።ለምን አላደርገውም ብዬ ፍላጎቴን በመከተል የእግር ኳስ ጨዋታን ደንብ መማር ጀመርኩ" ስትል የእግር ኳስ ዳኝነት ትምህርት የጀመረችበትን ጊዜ ታስታውሳለች። ይኼ ድርጊቷ ካልተዋጠላቸውና፤ በበጎ ጎኑ ካልተመለከቱት ውስጥ ደግሞ፤ ወንድሞቿ ቀዳሚዎች ነበሩ። "በምኖርበት ከተማ አንድ ሴት አጭር ቁምጣ ለብሳ ከወንዶች ጋር ሥልጠና ስትወስድ መታየቷ፤ እንደ አሳፋሪ ድርጊት ስለሚታይ መነጋገሪያ ሆኜ ነበር" ትላለች። የቦችራ ካርቡቢ የዳኝነት ጉዞ እንደ አውሮፓውያን ቆጣጠር በ2007፤ ሞሮኮ ብሔራዊ የሴቶች እግር ኳስ ሻምፒዮናን ጀመረች። ይህ መሆኑ ቡችራ ካርቡቢ ብሔራዊ ዳኛ እንድትሆን ዕድል የፈጠረላት ሲሆን፤ መኖሪያዋንም ከትውልድ ሥፍራዋ "ታዛ" ወደ ሞሮኮ ሌላኛዋ ከተማ "ሚከንስ" እንድትቀይር አደረጋት። "ይህን ዕድል ማግኘቴ ቤተሰቦቼ እንዲረዱኝና ሙያዊ ለሆነ ጉዳይ እንደምሄድ እንዲያምኑ አድርጓቸዋል" በማለት የዳኝነት ሙያዋን በመጨረሻ እንደተቀበሉት ታስረዳለች። በሚከንስ ከተማ በእግር ኳስ ዳኝነት ሥልጠና ላይ እያለች፤ አንድ ቀን አባቷ መጥቶ እንደተመለከታትና፤ ወንድሞቿ ምርጫዋን ሊያከብሩላት እንደሚገባ እንደነገራቸውም ገልፃለች። የ19 ዓመት ወጣት እያለችም፤ በሞሮኮ የሴቶች አንደኛ እና ሁለተኛ የሊግ ውድድር በመዳኘት፤ የዳኝነት ሥራዋን አንድ ብላ ጀመረች። ይህ ከሆነ ከ10 ዓመት በኋላ፤ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2016 ደግሞ፤ ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ ዳኛ በመሆን ራሷን ወደ ሌላ ምዕራፍ አሸጋገረች። ከሁለት ዓመት በኋላም በ2018 በጋና አስተናጋጅነት በተከናወነው የሴቶች የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር ፤ በዛምቢያና በኢኳቶሪያል ጊኒ መካከል የተደረገውን ጨዋታ በመሀል ዳኝነት አጫወተች። ይህም በአህጉራዊ የውድድር መድረክ ለመጀመሪያ ጊዜ በመሀል ዳኝነት ያጫወተችው ጨዋታ ሆኖ ተመዘገበላት። እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2020፤ "ቦቶላ" እየተባለ በሚጠራው በሞሮኮ የወንዶች ከፍተኛ የሊግ ውድድር ላይ በመሀል ዳኝነት በመዳኘት፤ የመጀመሪያዋ ሴት ሆነች ። ከአንድ ዓመት በኋላም በካሜሮን አስተናጋጅነት በተከናወነው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፤ ሴኔጋልና ግብፅ ባደረጉት የፍፃሜ ጨዋታ የቫር ዳኛ (video assistant referee) በመሆን ሰርታለች። ከዛሬ ሁለት ዓመት በፊትም የሞሮኮ የንጉሱ ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታን በመዳኘትም ቀዳሚዋ ሴት ናት። አሁን ላይ እየተከናወነ ባለው 34ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ወድድርም፤ በጊኒ ቢሳውና በናይጄሪያ መካከል የተከናወነውን ሦስተኛ የምድብ ጨዋታ በመሀል ዳኝት በመምራት፤ የመጀመሪያዋ ሰሜን አፍሪካዊት የአረብ ሴት ሆናለች። ቡችራ ካርቡቢ ከእግር ኳስ ዳኝነት ሥራዋ በተጨማሪ፤ የፖሊስ ኦፊሰር በመሆን ሀገሯን እያገለገለች ትገኛለች።      
ዕልፍ ውበት ከኮይሻ ዕልፍኝ
Dec 23, 2023 2388
ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ፣ የቱባ ውበቶች መገለጫ ናት። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እንዳሉትም ፈጣሪ በሰጣት የተፈጥሮ ሀብት የታደለች ናት በተለይም በተራሮች፣ በሸለቆዎች፣ በወንዞችና በሐይቆች፣ የተሞላች ሀገር ናት። በአንድ በኩል ተፈጥሮ በብዙ ያደላት፣ ልጆቿም በትጋታቸው በየዘመናቱ ያደመቋት ብትሆንም በሌላ በኩል በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ፈተናዎች እንዲሁም በመሰረተ ልማት መጓደል ፀጋዎቿን በአግባቡ ሳታስተዋውቅና ሳትጠቀምበት ቆይታለች። ከአምስት ዓመታት በፊት የመጣውን አገራዊ ለውጥ ተከትሎ መንግስት ለብዝሃ ኢኮኖሚ በሰጠው ትኩረት ቱሪዝም አንዱ የኢኮኖሚ ምሰሶ ሆኖ ብቅ ማለቱን ተከትሎ ጸጋዎቿ እየተገለጡ ይገኛሉ። በዚህም የአገሪቱን የቱሪዝም አለኝታዎች በአግባቡ መለየትና ማልማት፣ የቱሪዝም መዳረሻዎችን መሠረተ-ልማት ማጠናከርና ተጨማሪ አዳዲስ መሠረተ-ልማቶችን መገንባት የመንግስት የትኩረት አቅጣጫዎች ሆነዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በገበታ ለሸገርና በገበታ ለሀገር ፕሮጀክቶች ውጤታማ የቱሪዝም ልማት ስራዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ዕውን ሆነዋል። በገበታ ለሸገር ከተገነቡና ለአገልግሎት ከበቁ የቱሪዝም መዳረሻዎች መካከል የእንጦጦ፣ የአንድነትና የወዳጅነት ፓርኮች ይጠቀሳሉ። በወንዝ ዳርቻ ልማትም ሰፋፊ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። በገበታ ለሀገርም ጎርጎራ፣ ወንጪ-ደንዲና ኮይሻ ፕሮጀክቶች ተጠቃሽ ናቸው። የኢትዮጵያን ውብ የተፈጥሮ ብልጽግና ሰዎች አይተው ይረኩ ዘንድ የኮይሻ ፕሮጀክት ውብ ሆኖ መሰናዳቱን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከሰሞኑ በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው አጋርተዋል።   የኮይሻ የገበታ ለሀገር ፕሮጀክት የብዝኃ-ቱሪዝም ባለቤት ለሆነችው ኢትዮጵያ ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር ነው። የኮይሻ ኢኮ-ቱሪዝም በውስጡ ከያዛቸው በርካታ ሀብቶች መካከል የጨበራ ጩርጩራ ፓርክ አንዱ ሲሆን በማራኪ ጥብቅ ደን የተሸፈነ ብሔራዊ ፓርክ ነው። በገበታ ለአገር በኮይሻ ፕሮጀክት ውስጥ ከሚለሙ የቱሪዝም መስህቦች አንዱ የሆነው ጨበራ ጩርጩራ ብሔራዊ ፓርክ ለአረንጓዴ ቱሪዝም ሁነኛ ማሳያ የሚሆን የሀገሪቱ ታላቅ የመስህብ ስፍራ ነው። የመካከለኛው ኦሞ ሸለቆ አረንጓዴያማው ጌጥ ጨበራ ጩርጩራ ወደ 50 የሚጠጉ ከትናንሽ እስከ ትላልቅ ወንዞች መነሻ ሲሆን በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኙትን ጨምሮ አያሌ የዕፅዋት ብዝኃ ሕይወትን የለበሰ ተፈጥሯዊ ፀጋ ነው። የጨበራ ጩርጩራ ብሔራዊ ፓርክ ዝርያው እየተመናመነ የመጣው የአፍሪካ የዝሆን ዝርያን ጨምሮ እንደ ጎሽ፣ ዲፋርሳ፣ ከርከሮ፣ ሳላ እና አጋዘን ያሉ የዱር እንስሳት የሚገኙበት ነው፡፡ ፓርኩ በደን ሽፋኑ ይበልጥ ጎልቶ ስሙ የሚነሳ ሲሆን፤ በፓርኩ ውስጥ የሚያቋርጡ በርካታ ወንዞችና አምስት ሃይቆችም ይገኛሉ። በጉያው ካቀፋቸው ፏፏቴዎች መካከል ባርቦ ፏፏቴ አንዱ ሲሆን የፏፏቴው ድምጽ ለፓርኩ ተጨማሪ ድምቀት ሆኖታል። የገበታ ለአገር ፕሮጀክት አካል በሆነው የኮይሻ ፕሮጀክት ፓርኩን ለመጎብኘት የሚያስችል መሰረተ ልማት በማሟላት የአካባቢውን የቱሪዝም ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተለያዩ ስራዎች ተከናውነዋል። የመሰረተ ልማት ግንባታዎቹ የፓርኩን ተፈጥሮ ሳይረብሽ ከፓርኩ ውጪ የሚከናወን ሲሆን ይህም ቱሪስቶች ፓርኩን በቀላሉ እንዲጎበኙት የሚያስችል ነው።   ሌላው የኮይሻ ውብት የግልገል ጊቤ ሶስት ግድብ የፈጠረውን ሰው ሰራሽ ሀይቅ ተንተርሶ የሚገኘው ሀላላ ኬላ ነው። ሀላላ ኬላ በዳውሮ ዞን በኮረብታዎች፣ ሰንሰለታማ ተራራዎችና በግልገል ጊቤ 3 የኃይል ማመንጫ ግድብ የተከበበ ስፍራ ነው። በዳውሮኛ ቋንቋ "ኬላ" ማለት የድንጋይ ካብ ማለት ሲሆን ሃላላ ኬላ በ1532 ዓ.ም ተጀምሮ በ10 የዳውሮ ነገስታት ለ200 ዓመታት የተገነባ ነው። ስያሜውንም በመጨረሻው ንጉስ ሃላላ ስም ያገኘ ሲሆን ቅርሱ 500 ዓመታትን አስቆጥሯል። ስፍራው ፀጥታ የሰፈነበት፣ የተረጋጋና መንፈስን የሚያድስ እንዲሁም ታሪክ፣ ባህልና መልከዐ ምድርን ማድነቅ ለሚፈልጉ ማረፊያና ማራኪ የቱሪስት መስህብ እንደሆነ ይነገርለታል። ሀላላ ኬላ ሪዞርት የኢትዮጵያን የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ለማጎልበትና ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ መዳረሻ ለመክፈት በማሰብ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አማካኝነት በ2013 ዓ.ም ይፋ በሆነው የገበታ ለአገር ፕሮጀክት ስር ከሚገኙ የኮይሻ ቅርንጫፍ ስራዎች መካከል አንዱ ነው። በርካታ የተፈጥሮ በረከቶች በአንድ ቦታ የሚገኙበት ሀላላ ኬላ ጎብኚዎች የሚመኙት አይነት አካባቢ፤ የሚውዱት አይነት የተረጋጋ የአየር ጠባይ ያለው ነው፤ የሀላላ ኬላ ሪዞርት። ሪዞርቱ የተገነባው ኢትዮጵያ ያሏትን ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ ሀብቶች በማጎልበት ማራኪነታቸውንና መስህብነታቸውን በመጨመር እንዲሁም ተደራሽነታቸውን በማስፋት ለእይታ እንዲበቁ ለማድረግ ነው። በተጨማሪም ወደ ስፍራው የሚያቀኑ ጎብኚዎች በእንቅስቃሴያቸው ሁሉ እንዲደሰቱና አዲስ ቆይታ እንዲኖራቸው ጥሩ እይታን ፈጥሮ አካባቢውን በሚገባ የሚያስተዋወቅ ነው። የሪዞርቱ ንድፈ ሀሳብ የሃላላ ኬላ ግንብና የአካባቢውን ሕዝብ ታሪክ እንዲሁም የቱሪዝም ሀብትን ከማክበርና ከመጠበቅ ጋር የተቆራኘ ነው። ቱኩል በመባል በአካባቢው ነዋሪ የሚታወቀውን ባህላዊ የስነ ሕንጻ አሰራር ጥበብ በመከተል የቤቱ ውስጣዊ ክፍል አየር በደንብ እንዲያገኝ፣ ጣሪያቸው ከፍ ብሎ ተሰርቷል። የሃላላ ኬላ ሪዞርት በሚያዚያ ወር 2015 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይን ጨምሮ የተለያዩ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ ባለሀብቶችና እንግዶች በተገኙበት መመረቁ የሚታወስ ነው። የኮይሻ እልፍኝ ሌላው ውበት የሆነው የልማት ስራ የኮይሻ የሃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ነው። የፕሮጀክቱ የግንባታ ሂደት 62 በመቶ መድረሱን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ገልጸዋል፡፡ "በቅርብ ርቀት በጨበራ ጨርጩራ ብሔራዊ ፓርክ የሚገኘውን የጨበራ የዝሆን ዳና ሎጅን በምንመርቅበት በአሁኑ ወቅት የኮይሻ ግድብ ለአካባቢው የቱሪዝም ዕድል ተጨማሪ አስተዋፅኦ ያደርጋል" በማለትም በኮይሻ እልፍኝ ዕልፍ ውበት ዕልፍ ዕድል መኖሩን ተናግረዋል፡፡  
የዱርና የቤት እንስሳቱ ቤተሰባዊ ፍቅር
Dec 3, 2023 1381
በፍሬዘር ጌታቸው (ወላይታ ሶዶ ኢዜአ) አብዛኛውን ጊዜ አንዳንድ የዱር እንስሳት ለሥጋቸው፣ ለቆዳቸው፣ ለጥርሳቸው ወዘተ እየተባለ እንደሚገደሉ የአደባባይ ምስጢር ነው። መንግሥት ይህንን ጥቃት ለመከላከል የተለያዩ የዱር እንስሳት ፓርኮችን በማቋቋም ጭምር የተለያዩ እርምጃዎችን ሲወስድ ይታያል። እርምጃው የዱር እንስሳቱን ከመጥፋት እንዲሁም መንግስት ዘርፉን በማስጎብኘት የሚያገኘውን ጥቅም ከመጨመር ባሻገር ሊኖረው የሚችለው ፋይዳ ብዙ ነው። የዱር እንስሳቱ ለአካባቢ ሥነ-ምህዳር የሚያበረክቱት አስተዋፅኦ ሳይዘነጋ ማለት ነው። ሆኖም ግን አሁንም በሀገራችንም ሆነ በሌላው ዓለም የዱር እንስሳት በሰው ሰራሽም ሆነ የተፈጥሮ አደጋ ስጋት ላይ ናቸው። ለዛሬ የፅሁፌ ማጠንጠኛ የዱር እንስሳቱ ስጋትና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሳይሆን እነሱን በማላመድ ያልተለመደ ተግባርን እየፈፀመ ባለ ግለሰብ ላይ ይሆናል። ግለሰቡ ወጣት በረከት ብርሃኑ ይባላል፤ የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪ ነው። ወጣት በረከት አዘወትረን የምንሰማውን 'እንኳን ሰው ወፍ ያለምዳሉ' የሚለውን ብሂል በሚያስረሳ መልኩ እሱ አባባሉን 'እንኳን ሰው አውሬ ያለምዳሉ' ወደሚለው ቀይሮታል ማለት ይቻላል። በረከት “በጎሪጥ የሚተያዩ የዱር እንስሳትን በፍቅር እንዲኖሩ ያደረገበትን ሁኔታ በርካቶች በግርምት ሲመለከቱት ይታያል። የሰው ልጆች በተፈጥሮ ክፉ ሆነው አይወለዱም ዳሩ ግን በህይወት አጋጣሚ ከሚቀስሙት ክፉ ባህሪ የሚማሩትና የሚዋሃዱበት እንጂ ይላል በረከት። ''አብሪያቸው ለመሆን በመወሰኔ እውነተኛ ፍቅርን ከዱር እንስሳቱ ተምሬያለሁ'' የሚለው ወጣት በረከት ከሰባት ዓመት በፊት የዱርና የቤት እንስሳትን በተለይም ሰው ለመቅረብ የሚፈራቸውን ጭምር እንደ ዘንዶ፣ ጅብ፣ ዝንጀሮ፣ አዞ፣ ጦጣ፣ አሳማ እንዲሁም ውሻና የመሳሰሉትን በማሰባሰብ በአንድ ላይ እንዲኖሩ እያደረገ በአንድ ላይ ማኖር እንደጀመረ ይናገራል።   በዚህም ምክንያት ሰው ሰራሽ ሐይቅን በውስጡ የያዘ የወጣቶች መዝናኛ ፓርክ በወላይታ ሶዶ ከተማ ማቋቋሙን ገልጿል። የዱር እንስሳቱን ከአባያ ብላቴ እንዳመጣቸው የሚናገረው በረከት በይበልጥ ግን በመኪናና መሰል አደጋዎች የተጎዱ የዱር እንስሳትን ከወደቁበት በማንሳት እንዲያገግሙ ለማድረግ በሚያደርግላቸው የእንክብካቤ ቆይታ ታዲያ የዱር እንስሳቱ ከቤት እንስሳት ጋር አብረው የማደር፣ አብረው የመዋል፣ አብረው የመብላት፣ በአንድ ላይ የመጫወት ዕድሉን እንዳገኙ ነው ለኢዜአ የተናገረው። የቤትና የዱር እንስሳቱ ህብረትና አንድነት የሚያስቀና እንደሆነም ወጣት በረከት ገልጿል። ኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ የዱር እንስሳት ሀብት እንዳለ የሚናገረው ወጣት በረከት በውስጡ ለተፈጥሮ ያለውን ፍቅር ወደ ስራ መቀየሩን ነው የገለፀው። ከሌሎች የዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ጋር በመሆን ስራውን ለመሥራት ወስነው በመግባታቸው የከተማው አስተዳደር የሥራ ቦታና መነሻ ካፒታል እንደረዳቸው ገልፆ በዚህም በመበረታታት ያልተለመደ የስራ ዘርፍ ለመፍጠር ወጥነው መጀመራቸውን ይናገራል። ስራውን ሲጀምር ቀላል ሁኔታ እንዳልገጠመው ያስታወሰው በረከት "ካባ ድንጋይ የሚፈነቀልበትን ስፍራ አልምቶና ችግኝ ተክሎ ወደ ዛፍ መቀየር እንዲሁም የሰው ሰራሽ ሐይቅ እንዲያመነጭ ማድረግ የማይቻል ይመስላል" ይላል። ቦታውን በባለሙያ በማስጠናትና ደባል አፈር ከሌላ ቦታ በማስመጣት ህልማቸውን እውን ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት ማድረጋቸውን አውስቶ ዓላማቸውን ለማሳካት የሄዱበት ርቀት ለሌሎች አስተማሪ መሆኑንም ይናገራል። ቦታውን አሁን ላይ የተለያዩ የዱርና የቤት እንስሳት በጋራ የሚኖሩበትና በርካታ የአገር ውስጥና ከሌላው ዓለም የሚመጡ ጎብኚዎች የሚዝናኑበትና የሚያርፉበት "ጁኒየር የወጣቶች መዝናኛ ፓርክ" መክፈት መቻላቸውን ነው የተናገረው። እንስሳቶች የሚሰጣቸውን ስያሜ ሳይሆን ተቀራርበው የሚኖሩበትን የፍቅር ህይወት ለማየት የሚመጣው ጎብኚ የቆይታ ጊዜ እንዲራዘም ማድረግ እንዳለበት በማመን የማረፊያ ቤቶች እና ተጨማሪ መዝናኛዎችን በማስፋፋት አሁን ላይ ጥሩ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ አብራርቷል። በዚህም ''በፓርኩ ግቢ ውስጥ የወላይታ ሶዶ ከተማን ገጽታ የሚያሳይ ባለ ሰባት በር መግቢያና መውጫ ያለው ሆቴልና የጀልባ መዝናኛ አገልግሎት ለተጠቃሚዎች በመስጠት የተሻለ ስራ በመስራት ላይ እንገኛለን'' ብሏል። ፓርኩን ለመጎብኘት ለሀገር ውስጥ ጎብኚዎች ለአንድ ሰው 30 ብር፣ ለውጭ ዜጋ ደግሞ 100 ብር በማስከፈል አገልግሎት እየሰጡ ያነሳው ወጣቱ በአዘቦት ቀናት በቀን ከ400 በላይ ጎብኚ ፓርኩን እንደሚጎበኙ ፣ በሰንበት ቀናት እና በበዓላት ወቅት እስከ 1 ሺህ ድረስ ጎብኚዎች እንደሚመጡ ነው የተናገረው። ያንን ሁሉ አስቸጋሪ ጊዜ ለማለፍ ባደረጉት ብርቱ ጥረት ከቤተሰብና በጥቂቱም ቢሆን ከመንግሥት ጥገኝነት መላቀቃቸውን የሚናገረው ወጣቱ በህይወታቸው ጥሩ ኑሮ መኖር ከመጀመራቸውም በዘለለ በፓርኩ ውስጥ ላለው የእንስሳት እንክብካቤና ጎብኚዎችን የማስተናገድ ስራን ለሚያሳልጡ 22 ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር በመቻላቸውም ስኬታማ እንደሆኑም ያነሳል። "አሁን እንስሳቶቹ ቤተሰቦቼ ሆነዋል በአንድ ቅጥር ግቢ ውስጥ አብሬያቸው ውዬ ነው የማድረው ይላል። ስራ ሩቅ አይደለም አጠገባችን እንዲያውም እጃችን ላይ ነው ያለው የሚለው ወጣት በረከት ሆኖም ሌላ አካል መጥቶ እንዲሰጠን እንጠብቃለን፣ ይኸ አስተሳሰብ የእድገታችን ፀር ነው '' ሲልም አፅንኦት ሰጥቶታል። ኢትዮጵያ በዱር እንስሳት ሀብት በዓለም አቀፍ ደረጃ ስሟ የሚነሳ መሆኑን ጠቁሞ ሀብቱን ለማሳደግና ሳቢ በማድረግ ተደራሽነቱን ለማስፋት እንዲያመች የሎጅ ግንባታ ስራ እንቅስቃሴ ጀምሬያለሁ ባይ ነው። ፓርኩ ውስጥ 62 ምንጮች እንደሚገኙ የገለፀው ወጣት በረከት ማስፋፊያ ቦታ ቢሰጠው የተሻሉ ስራዎችን ለመስራት እቅድ እንዳለው ተናግሯል። በሰዎች ዓለም ውስጥ ገዢ ሀይል ፍቅር ሊሆን እንደሚገባ ፓርኩ ትልቅ የፍቅር ተምሳሌት ፓርክ ‼ ነው የሚሉት ደግሞ የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪ አቶ ታዲዮስ ታንቱ ናቸው። ፓርኩ በሂደት ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ስሟ እንዲጠራ ጉልህ ሚና ይኖረዋል የሚል ተስፋ እንዳላቸው በመግለጽ የሚመለከታቸው አካላት ተገቢውን ትኩረትና ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል። ፓርኩን ሲጎበኙ ያገኘናቸው የአዲስ አበባ ነዋሪው አቶ ለገሰ ቶማስ በበኩላቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየመነመነ ለመጣው የዱር እንስሳት ሀብት ማገገም የራሱን አስተዋጽኦ ሊያደርግ የሚችል ፓርክ መሆኑን ተናግረዋል። "ሁላችንም እንደዚሁ በእጃችን ያለውን ሀብት መጠቀም ካልጀመርን በቀር ሊለውጠን የሚመጣ ተዓምር አይኖርም'' ያሉት አስተያየት ሰጪው ከወጣት በረከት ሁሉም ብዙ ሊማር እንደሚገባም ጠቁመዋል።  
“ዮ-ማስቃላ''- ሁሉም የሚደሰትበት በዓል
Sep 23, 2023 1618
በሳሙኤል አየነው የሰላም፣ የአብሮነት፣ የፍቅር፣ የመቻቻልና የአንድነት ተምሳሌት የሆነው የጋሞ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል “ዮ-ማስቃላ” ከወርሃ መስከረም አጋማሽ ጀምሮ በተለያዩ ባህላዊ ሁነቶች በድምቀት ይከበራል ። በተለያየ ምክንያት በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ ተራርቀው የነበሩ ወገኖች ወደ የአካባቢያቸው በመመለስ ከቤተሰቦቻቸው ብሎም ከቀየው ህብረተሰብ ጋር አብረው የሚያከብሩት የዓመቱ ታላቅ በዓል ነው ። ታዲያ በዓሉን በድምቀት ለማክበር ወንዶች ሰንጋ በሬ ለመግዛት እንዲሁም ለትዳር አጋሮቻቸውና ለልጆቻቸው ልብስና ጌጣ ጌጥ የሚሆን ገንዘብ መቆጠብ የሚጠበቅባቸው ሲሆን ሴቶችም ለባህላዊ ምግቦች፣ ለቅመማ ቅመም፣ ለቅቤና ለባህላዊ መጠጦች እህል ግዥ የሚሆን ገንዘብ ዓመቱን ሙሉ ሲቆጥቡ ይከርማሉ። መስከረም ወር ከገባበት ዕለት አንስተው ወንዶችም ሆኑ ሴቶቹ በቆጠቡት ገንዘብ በየፊናቸው ለበዓሉ የሚሆኑ ቁሳቁሶችን ማቅረብ ይጀምራሉ። ይህም የዝግጅት ጊዜ “እንግጫ” በመባል ይጥራል። በ”ዮ--ማስቃላ” ጊዜ አብሮነት እንጂ ግለኝነት የሚባል ነገር በጋሞዎች ዘንድ ፈጽሞ አይታሰብም፤ አብሮ እርድ ማካሄድ፣ አብሮ መመገብ፣ አብሮ መጠጣት፣ አብሮ መጫወት የጋሞዎች መገለጫ ነው። እንደ ሌሎቹ በዓላት ሁሉ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖችም በዓሉን እንዴት እናሳልፍ የሚል ስጋት አያድርባቸውም። ምክንያቱም የሌለውም ካለው ጋር አብሮ የሚቋደስበት፣ የሚደሰትበት፣ የሚተሳሰብበትና የሰብአዊነት ልክ የሚንጸባረቅበት ልዩ ድባብ ያለው በዓል ነውና ዮ-ማስቃላ ። የጋሞ የሀገር ሽማግሌ አቶ አመሌ አልቶ ስለ “ዮ--ማስቃላ” በዓል በትንሹ እንዲያወጉን ጠይቀናቸው በዓሉ ለሰው ልጆች ብቻ ሳይሆን እንስሳትና አዕዋፋት ሁሉ የሚደሰቱበት እንደሆነ ነግረውናል። በአካባቢው ቋንቋ ተፈጥሮ ሁሉ በዓሉን በደስታ እንደሚያሳልፍ ለመግለጽ “ካፎስ ካናስ ማስቃላ” በማለት የሚገለጽ ስሆን “ለሰው ብቻ ሳይሆን ለእንስሳትም መስቀል ነው” እንደማለት ነው ብለዋል። በዓሉ ከመድረሱ ከሶስት ወራት አስቀድሞ በየአካባቢው ለእንስሳት የግጦሽ ሥፍራ ተከልሎ የሚዘጋጅ ሲሆን ችቦው በሚለኮስበት በደመራው ዕለት የቤት እንስሳት በሙሉ በዚያው የሚሰማሩ ይሆናል። ዓመቱን ሙሉ ሲያርሱ የነበሩ የእርሻ መሣሪያዎችም በበዓሉ ጊዜ ታጥበውና በቅቤ ታሽተው በክብር ይቀመጣሉ። ክብር ለሰው ልጆች ብቻ ሳይሆን ለእንስሳትና ለእርሻ መሣሪያዎችም ይሰጣል። በባህሉ መሠረት ችቦ በሚወጣበት ሰዓት አባት የራሱን ችቦ ለኩሶ የቤቱን ምሰሶ፣ የከብቶችን ጋጣና የበር ጉበኖችን ግራና ቀኝ በችቦው ጫፍ በማነካካት ወደ ውጭ ካወጣ በኋላ ወንድ ልጆች የየራሳቸውን ችቦ ተራ በተራ እየለኮሱ አባታቸውን ተከትለው “ዮ---ማስቃላ” እያሉ ወደ ደመራ ቦታ ያመራሉ። ከዚያም አባት በቅድሚያ ችቦውን ከለኮሰ በኋላ ልጆች ደግሞ ተከትለው ደመራውን ይለኩሳሉ። ከዚህ ፕሮግራም መልስ ወደ ቤት ተመልሰው የተዘጋጀውን ገንፎ በአንድ ወጭት ላይ “ዮ--ማስቃላ”እያሉ ሁሉም የቤተሰብ አባላት፣ ዘመድ አዝማድና ጎረቤት ተሰባስበው በጋራ ይመገባሉ። በ”ዮ--ማስቃላ” በዓል በዋናነት እርድ የሚከወን ሲሆን ቁርጥ፣ ጎረድ ጎረድ፣ ክትፎና የወጣ ወጥ ዓይነቶች ተሠርተው ለምግብነት ይቀርባሉ። ከባህላዊ ምግቦች ደግሞ የገብስ ቅንጬ፣ የቆጮና ገብስ ውህድ ቂጣ፣ የቡላ ፍርፍር፣ ሀረግ ቦዬ፣ እንዲሁም ከመጠጥ አይነቶች ደግሞ ቦርዴ፣ ጠላ፣ የማርና የቦርዴ ጠላ ውህድና ሌሎች ተወዳጅ ምግቦችና መጠጦች ይዘጋጃሉ። በ”ዮ--ማስቃላ” በዓል ዕለት የሚቀራረቡ ጎረቤታሞች በጋራ ሆነው አማካይ በሆነ ሥፍራ ላይ የእርድ ሥነሥርዓት ያከናውናሉ። የእርድ ሥነ-ሥርአቱም በደመራው ዕለትና ማግስት እንደ ህብረተሰቡ ይሁንታ የሚፈጸም ይሆናል። ከማግስቱ ጀምሮ የተዘጋጀውን ሥጋ በጋራ እየበሉና እየጠጡ የበዓሉን ድባብ የሚያስቀጥሉ ሲሆን “ዱንግዛ” በተሰኘው የጋሞ ባህላዊ ጥበብ ልብስ ደምቀው በጌጣጌጥ አሸብርቀው ሁሉም በየአደባባዩ በባህላዊ ጫዋታዎች እየተደሰተ በዓሉን ያከብራል። ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነትና አብሮነት ካለ በአዲሱ ዓመት ምድሪቱ ተገቢውን ምርት እንደምትሰጥ ሁሉም ሰው በተሰማራበት መስክ ውጤታማ እንደሚሆን ይታመናል። ከዚም የተነሳ በአሮጌው ዓመት ሃዘን ላይ የነበሩ ወገኖች ሙሉ በሙሉ ሀዘናቸውን በመተው በአዲስ መንፈስ ወደ መደበኛው ህይወት ይመለሳሉ። የተጣሉ ወገኖች ቂም ይዘው አዲስ ዓመትን መሻገር በጋሞዎች ዘንድ ነውር በመሆኑ በባህላዊ ሸንጎ ሥርአት /ዱቡሻ/ በጋሞ አባቶች አሸማጋይነት እርስ በርስ ተነጋግረው በመታረቅ አዲሱን ዓመት በጋራ ያበስሩታል። በሌላ መንገድ “ዮ..ማስቃላ” በዓል ተጠብቆ ወጣቶች የሚተጫጩበት፣ የተጫጩት ደግሞ ጋብቻ የሚከውኑበት እንዲሁም ያገቡት በየገበያው ዕለት “ሶፌ” የሚባል ሥነ-ሥርዓት በማከናወን በማህበራዊ ህይወት ማህበረሰቡን በይፋ የሚቀላቀሉበት መሆኑን ጋሽ አመሌ አውግተውናል። ጋሞዎች ከሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች ጋር በመሆን በአብሮነት ለሁለት ሳምንታት በደስታ ካሳለፉ በኋላ ወደ ግብርና ሥራቸው በመመለስ ቀደም ሲል በክብር ያስቀመጧቸውን የእርሻ መሣሪያዎች በማንሳት ወደ እርሻ ሥራ ይገባሉ። እስከ ታህሳስ ወር መውጫ ድረስ የበዓሉ ድባብ ሳይጠፋ ይቆይና በመጨረሻም የመሰናበቻ ድግስ ወይም “ጮዬ ማስቃላ” በማዘጋጀት በህብረት ከተመገቡና ከጠጡ በኋላ የዓመት ሰው ይበለን፣ ዓመቱ የሰላም፣ የጤና፣ የበረከት ይሁን በማለት በመመራረቅ “ዮ--ማስቃላ”ን ይሸኛሉ። በዓሉ የህዝቡን ሰላም ፣አንድነትና አብሮነት የሚያንጸባርቅ ልዩ በዓል ነው በማለት የጋሞ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ አቶ ሞናዬ ሞሶሌ የጋሞ የሀገር ሽማግሌ የሆኑት የአቶ አመሌ አልቶን ሃሳብ ይጋራሉ። ባህላዊ እሴቱ ከትውልድ ወደ ትውልድ ተጠብቆ እንዲቆይ “ዮ--ማስቃላ” ትልቅ ድርሻ አለው። የባህል እሴቶች ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፉ በጥናትና ምርምር በማስገፍና የቋንቋና ባህል አውደ ጥናት በየዓመቱ እየተደረገ እንደሆነም ነግረውናል። አባቶች በልዩነት ውስጥ ያለንን አንድነት እንዳቆዩልን ሁሉ ወጣቶችም ኢትዮጵያዊ ለዛ ያላቸው የጋራ እሴቶች ሳይበረዙና ሳይከለሱ ጠብቀው ለትውልድ የማስተላለፍ ሃላፊነት አለባቸው የሚለውን የንግግራቸው ማሳረጊያ አድርገዋል።              
የዕልፍ ሕጻናትን ዕጣ ፈንታ ከሞት ወደ ሕይወት የለወጠው ወጣት ላሌ ላቡኮ 
Sep 8, 2023 1817
በሀገራችን በርካታ አካባቢዎች የታዳጊዎችን ተስፋና ህልም ብቻ ሳይሆን ሕልውና የሚገዳደሩ ከባህላዊ እምነት ጋር የተቆራኙ አይነተ ብዙ ጎጂ ባህላዊና ልማዳዊ ድርጊቶች እና ክዋኔዎች አሉ። ለአብነትም ደቡብ ኦሞ ዞን እንደ ካራ፣ ሀመርና ቤና ህዝቦች ዘንድ የተለመደው እና ከህጻናት ጥርስ አበቃቅል ጋር የተያያዘው ’ሚንጊ' የሚሰኘው ጎጂ ልማዳዊ ድርጊት ይጠቀሳል። በአካባቢው ልማድ በታችኛው ድድ ጥርስ የሚያበቅሉ እንስሳት ቅዱስ፣ በላይኛው ድድ ጥርስ የሚያበቅሉ እንስሳት ደግሞ ርኩስ የሚል ስያሜ ይሰጣቸዋል። ከዚህ ጋር በማገናኘትም የሚወለዱ ህጻናት የላይኛው የወተት ጥርሳቸው ቀድሞ የሚበቅል ከሆነ እንደ እርኩሳን እንስሳት ከመጥፎ መንፈስ ጋር ተቆጥሮ ለማህበረሰቡ የማይበጅ፣ አድጎም ለቤተሰቡ ጠንቅ ተቆጥሮ የመገደል ዕጣ ፈንታ ይገጥመዋል። ይህ ልማድ “ሚንጊ” ተብሎ የሚጠራ ሲሆን አያሌ ህጻናትን ቀጥፏል። ይህ ብቻም ሳይሆን የማህበረሰቡ አባል ሴት ከትዳር በፊት ልጅ ከወለደች የተወለደው ሕጻን በ'ሚንጊ'ነት ይፈረጃል። ሚንጊ ተብለው የተፈረጁ ህጻናት በማህበረሰቡ ዘንድ መርገምት፣ ቁጣ፣ ርሀብ በሽታ… እንደሚያመጡ ስለሚቆጠር ከጥልቅ ወንዝ መጣል፣ ወደ ገደል መወርወር አልያም በጫካ ውስጥ የመጣል ዕጣ ይገጥማቸዋል። ሚንጊንና መሰል በየማህበረሰቡ ዘንድ ለዘመናት የተለመዱ ጎጂ ድርጊቶችን ለማስቀረት እና ማህበረሰብ አቀፍ ለውጥ ለማምጣት ግን ውስብስብ እና ጊዜ የሚጠይቅ ጉዳይ ነው። ላሌ ላቡኮና መሰል ብርቱና አርቆ አሳቢ ሰዎች ግን ባደጉበት ብርቱ ጥረት የማህብረሰብን አስተሳስብ በመለወጥ ለዘመናት ለሚከወኑ ውስብስብ ችግሮችን መፍትኤ መስጠት ችለዋል። ላሌ ላቡኮ በተወለደበት ቀዬ እና አባል በሆነበት ደመ ከልብ ሆነው የሚቀሩ ህጻናትን ዕጣ ፈንታ ከወንዝ፣ ከገደልና ከጫካ ከመጣል ተርፈው ለወግና ማዕረግ እንዲበቁ አስችላል። በአጉል ባህል ሕይወታቸውን የሚነጠቁ ዕልፍ አዕላፍ ህጻናት ነፍስ እንዲዘሩ በማድረግ ትውልድ ያሻገረ፣ ማህበረሰብን የለወጠ አርበኛ ነው። ላሌ ላቡኮ ይህን ነባር ጎጂ ልማዳዊ ድርጊት ለመቃወምና መፍትሄ ለማምጣት ያነሳሳው ሁለት እህቶቹን ጨምሮ ምንም ነፍስ ያላወቁ ሕጻናት በሚንጊነት ተፈርጀው ሲቀጠፉ በማየቱና በመስማቱ እንደሆነ ይናገራል። ከ17 ዓመታት በፊት ‘ኦሞ ቻይልድ’ በሚል ባቋቋመው ድርጅት 'ሚንጊ' የተባሉ 58 ሕፃናትን ከገዳዮች ፈልቅቆ ከሕልፈት ወደ ሕይወት ለውጧል፣ ለቁም ነገር ለማብቃትም እያስተማራቸው ይገኛል።   እህቶቹን ጨምሮ የትውልድ መንደሩ ሕጻናትን ሕይወት ለመቀጠፍ የዳረጋቸው የሚንጊ ድርጊት የሚፈጸመው፣ በማህበረሰቡ ዕውቀት ማነስ ነው ብሎ ያምናል። በዚህም ይህን አስከፊ ድርጊት እና አስተሳሰብ ለመቀየር ቆርጦ በመነሳቱ ቤተሰቡን ጨምሮ ከማህበረሰቡ መገለል እስከ ማስፈራሪያ ጥቃቶች አስተናግዷል። እርሱ ግን ፈተናዎች ሳይበግሩት በዓላማው ጸንቶ፣ ትዕግስትና ብልሃት ተላብሶ ሸውራራ ማህበረሰብ አቀፍ አመለካከቶችን መስበር ችሏል። የሚንጊ ባህል አሁንም ሙሉ ለሙሉ እንዳልተቀረፈ የሚናገረው ላሌ፣ ስር ነቀል የአስተሳስብ ለውጥ ለማምጣት ለህብረተሰቡ አሁንም ብርቱ ግንዛቤ የመፍጠር ስራዎች እንደሚገቡ ገልጿል። ላሌ በመሰረተው ድርጅት ከሚማሩ ሕጻናት ባሻገር ከ300 በላይ ህጻናት ከቤተሰባቸው ዘንድ ሆነው ለመማር እንዲችለኩ ማድረጉንም ይናገራል። ሕፃናቱን ከሞት አፋፍ ታድጎ ከራሳቸው ሕልውና ባለፈ ለቁም ነገር እንዲበቁና ለሀገርና ለወገን የሚበጁ ሰዎች እንዲሆኑ በመስራቱ አዕምራዊ እርካታ እንደሚሰማው ይገልጻል። ላሌ የሚንጊን ጎጂ ድርጊት ከመታደጉ በተጨማሪ በደቡብ ኦሞ ትምህርት ቤት ገንብቶ ከ700 በላይ ተማሪዎችን እያስተማረ ይገኛል። ናሽናል ጂኦግራፊ፣ ቴድ ቶክ፣ የሰብዓዊ መብቶች ተቋም እና የበጎ ሰው ሽልማት ድርጅት የላሌን ትውልድ የመታደግ ተግባር ዕውቅና ከሰጡት ወስጥ ይጠቀሳሉ።
የ19ኛ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዎና ደጋሹ የቡዳፔስት ስታዲየም
Aug 22, 2023 1606
  የቡዳፔስቱ ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየም 700 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በሚጠጋ ገንዘብ ተገንብቶ ዝግጅቱን አሟልቶ እንዲያስተናግድ በሚያስችል ቁመና ላይ የደረሰው ከ19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዎና መጀመር ቀደም ብሎ ነው። የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከኦሊምፒክ ጨዋታዎች ቀጥሎ የሚጠቀስ ግዙፍ የሆነ ዓለም አቀፍ የስፖርት ሁነት ነው። “የስፖርቶች ንጉስ” የሆነ ውድድር ነው የሚሉትም አልጠፉም። አገራት ለሻምፒዮናው ከሚያደርጉት ሽር ጉድ ባለፈ እንደዚህ ዓይነት ስፖርታዊ ውድድሮችን ለማዘጋጀት የሚያደርጉት ፉክክር ቀላል የሚባል አይደለም። ዓለም አቀፍ የስፖርት ሁነቶችን ለማዘጋጀት ሚሊዮኖችን አለፍ ካለም ቢሊዮኖችን ወጪ ያደርጋሉ። አገራት ውድድሩን ከማስተናገድ ባለፈ ታሪካቸውንና ባህላቸውን ጨምሮ ያላቸውን መልካም ገጽታ ለመገንባት ይጠቀሙበታል ። 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከቀናት በፊት በማዕከላዊ አውሮፓዊቷ አገር ሃንጋሪ ተጀምሯል። በሻምፒዮናው ላይ ከ200 አገራት በላይ የተወጣጡ ከሁለት ሺህ በላይ አትሌቶች እየሳተፋ ይገኛሉ። ሻምፒዮናው ቡዳፔስት በሚገኘው ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየም በመካሄድ ላይ ይገኛል። ነሐሴ 13/2015 የሻምፒዮናው ደማቅ የመክፈቻ ስነ ስርዓት በዚሁ ስታዲየም ተከናውኗል። በመክፈቻ ስነ ስርዓቱ ላይ የሀንጋሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ቪክቶር ኦርባን፣የሀንጋሪ ፕሬዝዳንት ካታሊን ኖቫክ፣ የተርኪዬ ፕሬዝዳንት ሬሲፕ ታይብ ኤርዶጋን፣ የዓለም አትሌቲክስ ፕሬዝዳንት ሰባስቲያን ኮ፣የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ፕሬዝዳንት አሌክሳንዳር ሴፈሪንና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች መገኘታቸው ይትወሳል። እኛም ሻምፒዮናው እየተካሄደበት ስላለው ስታዲየም መረጃዎችን ልናካፍላችሁ ወደናል። ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየም የግንባታ መሰረት ድንጋይ እ.አ.አ በ2020 ተጥሎ ግንባታው የተጀመረው እ.አ.አ 2021 መግቢያ ላይ ነበር። ስታዲየሙ ግንባታው ከመጀመሩ በፊት 40 ሺህ ተመልካች እንደሚያስተናግድ ይፋ ተደርጎም ነበር። ይሁንና የግንባታው ስራ ሲጀመር በሚይዘው የተመልካች ብዛት ላይ ክለሳ ተደርጎ ስታዲየሙ 36 ሺህ ተመልካች በሚያስተናግድ መልኩ ግንባታው እንደሚቀጥል ተገለጸ። በዚሁ መሰረት የላይኛው የስታዲየም ክፍል 22 ሺህ እንዲሁም የታችኛው ክፍል 14 ሺህ ተመልካች እንዲደሚይዝ የሃንጋሪ መንግስት አስታወቀ። የስታዲየሙ ግንባታ ከእ.አ.አ 2022 አጋማሽ ዓመት በኋላ ተጠናቆ በዛው ዓመት ማብቂያ ለዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው የትኬት ሽያጭ መከናወን ጀመረ። ስታዲየሙ እ.አ.አ ሰኔ 16/2023 የዓለም አትሌቲክስ ፕሬዝዳንት ሰባስቲያን ኮን ጨምሮ ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ተመርቆ በይፋ ስራ ጀመረ። አጠቃላይ ለስታዲየሙ ግንባታ 700 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር የሚጠጋ ወጪ መደረጉንና ይህም ሀንጋሪ ለስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታ ያወጣችው ትልቁ ገንዘብ ሆኖ ተመዝግቧል። ከዚህ ቀደም ሀንጋሪ ለስፖርት መሰረተ ልማት ያወጣችው ትልቁ ወጪ ከ67 ሺህ በላይ ተመልካች ለሚያስተናግደው ፑሽካሽ አሬና ስታዲየም ሲሆን ለስታዲየሙ ግንባታ 600 ሚሊዮን ዶላር ፈሰስ እንደተደረገበት መረጃዎች ያመለክታሉ። የውድድሩ መሮጫ መም “The Crown of the Queen of Sports” የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲሆን ስያሜው የመነጨው አትሌቲክስ የሁሉ ስፖርቶች ቁንጮ ነው ከሚል እሳቤ መሆኑን ተገልጿል። ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየምን የገነቡት ‘ዛኤቭ ኢፕቶይፓሪ ዜድአርቲ’ (ZÁÉV Építőipari Zrt) ‘ማግያር ኢፒቶ ዜድአርቲ’ (Magyar Építő Zrt) የተሰኙ ተቋራጮች ናቸው። ስታዲየሙ የሚገኘው በደቡብ ማዕካላዊ ቡዳፔስት እና በአውሮፓ በትልቅነቱ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠው የዳኑብ ወንዝ ምስራቃዊ አቅጣጫ ነው። ከዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው በኋላ የስታዲየሙ የመያዝ አቅም ወደ 14 ሺህ ዝቅ እንደሚልና በተመልካቾች በኩል ያሉ ጊዜያዊ የስታዲየሙ የላይኛው ክፍል መሰረተ ልማቶች እንደሚነቀሉም ተገልጿል። የዓለም የአትሌቲክስ አፍቃሪያን በስታዲየሙ በቀጣይ ቀናት በሚካሄዱ የአትሌቲክስና የሜዳ ተግባራት ውድድሮችን በጉጉት መከታተላቸውን ይቀጥላሉ። የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው እስከ ነሐሴ 21/2015 ይቆያል። በሃንጋሪ ቡዳፔስት እየተካሄደ በሚገኘው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የአራተኛ ቀን ውሎ የኢትዮጵያ አትሌቶች የሚሳተፉባቸው ሁለት የፍጻሜ ውድድሮች ይካሄዳሉ። ከምሽቱ 4 ሰአት ከ30 የ1 ሺህ 500 ሜትር ሴቶች አትሌት ብርቄ ኃየሎም እና አትሌት ድርቤ ወልተጂ ይሳተፋሉ። አትሌት ብርቄ 3 ደቂቃ ከ54 ሴኮንድ ከ94 ማይክሮ ሴኮንድ እና አትሌት 3 ደቂቃ ከ55 ሴኮንድ ከ8 ማይክሮ ሴኮንድ በርቀቱ ያላቸው የግል ምርጥ ሰዓት ነው። በ3 ደቂቃ ከ49 ሴኮንድ ከ11 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት የሆነችው የ29 ዓመቷ ኬንያዊ አትሌት ፌዝ ኪፕዬጎን ውድድሩን የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት አግኝታለች። አትሌቷ የ1 ማይል እና የ5 ሺህ ሜትር የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤትም ናት። በዚህ ውድድር ላይ በትውልድ ኢትዮጵያዊ በዜግነት ኔዘርላንዳዊ የሆነችው አትሌት ሲፋን ሀሰን ትወዳደራለች። ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ42 ደቂቃ በ3 ሜትር መሰናክል ወንዶች ፍጻሜ የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት አትሌት ለሜቻ ግርማና አትሌት ጌትነት ዋለ ይወዳደራሉ። አትሌት ለሜቻ በሰኔ ወር 2015 በፓሪስ በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ ውድድር በ3 ሺህ ሜትር መሰናክል 7 ደቂቃ ከ52 ሴኮንድ ከ11 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት በኳታሩ አትሌት ሳይፍ ሰኢድ ሻሂን ለ19ኝ ተይዞ የነበረውን የርቀቱን ክብረ ወሰን በ1 ሴኮንድ ከ52 ማይክሮ ሴኮንድ ማሻሻሉ ይታወቃል። አትሌት ጌትነት 8 ደቂቃ ከ5 ሴኮንድ ከ15 ማይክሮ ሴኮንድ በርቀቱ ይግል ምርጥ ሰአቱ ነው። በውድድሩ አትሌት ለሜቻ እና የሞሮኮው አትሌት ሶፊያን ኤል ባካሊ የሚያደርጉት ፉክክር በስፖርት ቤተሰቡ ከወዲሁ በጉጉት ይጠበቃል። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው እስከ አሁን 1 የወርቅ፣1 የብር እና 2 የነሐስ በአጠቃላይ አራት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች።
ቡሄ እና ትውፊቱ
Aug 19, 2023 1369
  በአየለ ያረጋል "ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት" ዛሬ ማታ ለጠበል ጠዲቅ እንዳትቀር ሲሉኝ ጎረቤቴ ደብረ ታቦርን አስታወሱኝ። እኔ ባደኩበት ገጠራማ አካባቢ ዛሬን (ነሐሴ 13) ደብረ ታቦር እንለዋለን። ይህ ዕለት በአብዛኛው ኢትዮጵያ አካባቢ 'ቡሄ' በሚል ይታወቃል። የክረምት ወቅት ሦስተኛው ወርኅ ነሐሴ ነው። ቡሄ ደግሞ ከወርኅ ነሐሴ ውብ መልኮች አንዱ ነው። ትውፊታዊ አንድምታው ከክረምት ወደ ጥቢ፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከጭጋግ ወደ ወገግታ...የመሸጋገር ምኞት ጋር ይቆራኛል። "ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት" የሚባለውም ለዚህ ይመስላል። በገጠር በእርሻ ሲማስን የከረመ ለገበሬ እና በሬ ከቡሄ በኋላ እፎይታ ማግኘት ይጀምራል። የክረምቱን ከባድ ወቅት አልፎ ጳጉሜን ተሻግሮ ተናፋቂው ወርኅ መስከረም ለመድረስ ('ነይ ብራ ነይ ብራ' እንዲሉ) የቡሄ ወቅት የጉጉት ሰሞን ነው። አዲስ ዓመትን ለማየት የመሻት ምልክት ነው። በነሐሴ አጋማሽና መገባደጃ የአርሶ አደሩ ማሳ ቡቃያ ይለብሳል። ቡሄ መሠረቱ ሃይማኖታዊ ቢሆንም እንደየአካባቢው መልከ-ብዙ መንፈሳዊ፣ ባህላዊና ትውፊታዊ ክዋኔዎች አሉት። ቡሄ ታዳጊዎች ይናፍቁታል። በሃይማኖታዊ አስተምህሮው ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር (ታቦር ተራራ) ክብረ-መንግሥቱን እና ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ትዕምርት እንደሆነ ሊቃውንተ- ቤተክርስቲያን ይገልጻሉ። የቡሄ ክዋኔዎች እና ስነ-ቃሎች ሆያ…. ሆዬ….!ሆ….! ቡሄ መጣ በዓመቱ፣ ኧረ እንደምን ሰነበቱ እዛ ማዶ ጭስ ይጨሳል፣ አጋፋሪ ይደግሳል፤ ... የቡሄ ዕለት ማታ ችቦ ይበራል፡፡ ሕፃናቱ ጅራፍ ገምደው ያጮሃሉ። እናቶችም ስንዴ አጥበው እና ፈትገው ዳቦ ይጋግራሉ። ሙልሙል ያዘጋጃሉ። ቀዬው በሕፃናቱ ዜማ ድባብ ይሞላል። መንደሩ በ"ሆያ ሆዬ" ሕብረ- ዝማሬ ይደምቃል። "ቡሄ ና በሉ፤ ቡሄ በሉ ቡሄ መጣ፤ ያ መላጣ፤ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ …" በሚለው። ይህ ትውልድ ተሻጋሪ ትውፊት እሴቱና ልማዱ ቢለዋወጥም ዛሬም ይከወናል። ቡሄ ትርጉሙ 'ብራ' ማለት ነው። ከሙልሙል ዳቦ በማቆራኘትም 'መላጣ" ማለት ነው የሚሉም አሉ። የቡሄ ጭፈራ በሁሉም አካባቢዎች የተለመደ ነው። ሕፃናቱ ጨፍረው ሙልሙል ዳቦ ይቀበላሉ። ሙልሙል ሲሰጣቸው ምስጋና፣ ሙልሙል ካልተዘከሩ ደግሞ የሐሜት ስነ-ቃሎችን ያስከትላሉ። ለምሳሌ በቡሄ ጭፈራ ዳቦ ከቀረበላቸው "... ሐሚና ሚና፤ ዘነዘነና የበር ዘነዘና ጌታዬን ያማ ሰው፤ እከክ ይውረሰው..." ሲሉ ሙልሙል ያልጋገረች ሴት የተገኘች እንደሆነም "የቡሄ ዕለት ያልጋገረች ሴት፤ አንድ እግሯ ከቆጥ አንድ እግሯ ከረመጥ..." ይላሉ። በነገረ ትውፊት ጽሑፎች የሚታወቁት ካህሳይ ገብረእግዚአብሔር ስለ 'ብሂለ ወራት' ከጠቀሷቸው ስነ-ቃሎች መካከል ወርኅ ነሐሴ እንዲህ ተጠቅሷል። ... " በሐምሌ እንዴት እከርማለሁ ደግሜ በነሐሴ ነፍሴን እዣለሁ በጥርሴ .... ነሐሴን በእንጥርጣሪ፣ ሐምሌን በብጣሪ ነሐሴ እግር በረቱ፣ መስከረም ዳገቱ በግንቦት አተላ፣ በነሐሴ ባቄላ ..." የቡሄ በዓል የብርሃን በዓል ማለት ነው። የብርሃኑ መገለጥ ዕለት ነው። በዚህም ነሐሴ 13 አመሻሽ ችቦ ይለኮሳል። የችቦው ትዕምርት ደግሞ አንዱ ለሌላው መካሪ አስተማሪ፣ አርዓያ፣ ምሳሌ፣ ብርሃን መሆኑን ያመላክታል። የጅራፍ ትውፊታዊ መልኩ ሁለት ዓይነት ምስጢር ይሰጠዋል። ቀዳሚው ምስጢር የኢየሱስ ክርስቶስን ግርፋትንና ሞቱን ሲሆን ሁለተኛው የጅራፍ ነጎድጓድ ድምፁ የባሕርይ አባቱን (የአብን) ምስክርነት ይወክላል። ነገረ-ሙልሙልም የራሱ ትውፊታዊ ትርጓሜ አለው። በችቦ ብርሃን ወላጆች እረኝነት የወጡ ልጆቻቸውን ለመፈለግ ሲወጡ ለልጆቻቸው በያዙት ስንቅ ይመሰላል። የሙልሙል ዳቦ ዝክሩ መተሳሰብን፣ ፍቅርንና አብሮነትን ይወክላል። ዛሬም ዳቦ የሚጋገረው ለዚህ ትውፊት ነው። ታዳጊዎች 'ሆያ ሆዬ' እያሉ ሙልሙል ዳቦ የሚጠይቁትም ከዚህ ትውፊት የመነጨ ነው። በሌላ ጎኑ ሕፃናቱ በደቀመዛሙርት፣ ዝማሬያቸው ደግሞ በ 'የምሥራች' እንዲሁም ስጦታው በምርቃት ይመሰላል። በዓለ-ደብረ ታቦር ወይም በቡሄ ትውፊታዊ ክዋኔዎች የየራሳቸው ትርጓሜ እና እሴት ቢኖራቸውም አልፎ አልፎ ከትውፊት ያፈነገጡ ክዋኔዎች ይስተዋላሉ። በዚህም ነባሩ ትውፊት ወደ ትውልድ ወግና ሥርዓቱን ሳይለቅ በቅብብል መተላለፍ እንዳለበት የሚሞግቱ ሰዎች ጥቂት አይደሉም። ለምሳሌ ጅራፍን በርችት መተካት 'የምስጢር ተፋልሶ አለው፤ ማኅበራዊ ገጽታው አይበጅም' የሚሉ ወገኖች አሉ። በሆያ ሆዬ የሚሰሙ ግጥሞች ከግብረ-ገብነት ያፈነገጡ፣ ዓለማዊ መልዕክት ያላቸው፣ ስድብ፣ ፌዝና ሥላቅ ይዘት ያዘሉ ሆነው እንደሚስተዋሉ በመጥቀስ ይህን ተግባር አጥብቀው ይተቻሉ። በሌላ በኩል በሙልሙል ዳቦ የተጀመረው እና ሃይማኖታዊ አንድምታ የነበረው የታዳጊዎች 'ሆያ ሆዬ' ትውፊታዊ ሥርዓቱን እየለቀቀ ገንዘብ መሰብሰቢያ መሆን እንደሌለበት ይነሳል። በቡሄ ምሽት በከተሞች አካባቢ የሚስተዋል የመጠጥና ስካር ድባብም እንዲሁ። ይልቁንም ለነዳያን እየዘከሩ እና እየዘመሩ በሰፈር ማኅበራዊ አብሮነት የሚያሳዩ ወጣቶችን ማበረታታት እንደሚገባ ይመክራሉ። መልካም ቡሄ!!          
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም