መጣጥፍ - ኢዜአ አማርኛ
መጣጥፍ
የሀመሯ እናት- የደስታ እንባ
Sep 11, 2025 377
የሀመሯ እናት- የደስታ እንባ በጣፋጩ ሰለሞን (ከጂንካ) በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገኘው ሐመር ወረዳ የሐመር ብሔረሰብ ዘመን በተሻገሩ ባህላዊ ሥርዓቶች ይታወቃል። በዚህ አካባቢ ከሚዘወተሩትና በብዛት ከሚታወቁት ባህላዊ ሥርዓቶች መካከል “ኢቫንጋዲ እና ኡኩሊ” የተባሉ ባህላዊ ጨዋታዎች ይጠቀሳሉ። “ኡኩሊ”በሐመሮች ዘንድ በስፋት የሚታወቅ ባህላዊ ጨዋታ ሲሆን ለአቅመ አዳም የደረሰና ከብት ለመዝለል ዝግጁ የሆነ የሐመር ወጣት የሚጠራበት የማዕረግ ስም ነው፡፡ “ኡኩሊ” ከብት በሚዘለልበት ዕለት ሥርዓቱ በሚፈጸምበት ሥፍራ ላይ በቅርብም ይሁን በሩቅ ያሉ የወጣቱ ዘመዶች ተጠርተው የሚከናወን ባህላዊ ሥርዓት መሆኑ ይታወቃል። “ኢቫንጋዲ” ደግሞ በሐመሮች ዘንድ በስፋት የሚታወቅ ባህላዊ ጭፈራ ሲሆን ትርጉሙም “ኢቫን” ማለት “ ማታ” ሲሆን “ጋዲ” ማለት ደግሞ “ጭፈራ” ማለት መሆኑ ይነገራል። ኢቫንጋዲ በአዝመራና በደስታ ወቅት በሥራ የደከመን አእምሮና አካል ለማዝናናት ሲባል የሚከናወንና የሀመር ወጣቶች በጉጉት የሚጠብቁት ባህላዊ ጭፈራ ነው። በዚህ ባህላዊ ጨዋታ ላይ የሐመር ወጣት ወንዶችና ልጃገረዶች አምረውና ተውበው በጨረቃ ብርሃን ይጨፍራሉ። የኢቫንጋዲ ጭፈራ በሶስት ቀን አንድ ጊዜ በሐመር መንደሮች በምሽት ከጨረቃ ድምቀት ጋር አብሮ ይደምቃል። “በጨረቃ ብርሃን አየኋት በማታ ኢቫንጋዲው ቦታ” የተባለላቸው የሃመር ውብ ልጃገረዶችም ከጨረቃ ብርሃን ጋር ደምቀው የሚታዩበት ዕለት ይሆናል። በወጣትነታቸው በዚሁ ባህላዊ ሥርዓት ያለፉት የሀመሯ እናት- ወይዘሮ ባሎ ኡርጎ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ እናት ናቸው። በሐመር ወረዳ ዲመካ ከተማ የሚኖሩት ወይዘሮ ባሎ፤ በደሳሳ ጎጇቸው ሲያገኙ በልተው ሲያጡ ደግሞ ኩርምት ብለው ያሳለፉባቸው ጊዜያት እንዳሉ ያስታውሳሉ። በደሳሳ ጎጆ እየኖሩ ዝናብ ሲመጣ የጎርፍ፣ ብርድና ዶፉ ስጋት ላይ ጥሏቸው እንደኖሩ ያነሳሉ፤ በበጋ ወራት ደግሞ የሚነፍሰው ነፋስና ሀሩሩ ጸሃይ ይፈትናቸው እንደነበር ይናገራሉ። ከእለታት አንድ ቀን ወጣቶችና ጎልማሶች ጭምር ሰብሰብ ብለው መጥተው “ቤትዎን በነፃ ልናድስልዎት ነው ሲሉኝ አላመንኳቸውም ይላሉ። የእውነታችሁን ነው አልኳቸው? አዎን ቤትዎን አፍርሰን ልንሰራልዎት ነው” ብለው አረጋገጡልኝ በማለት ሁኔታውን በደስታ እንባ ታጅበው ያስታውሳሉ። በተባለው መሰረትም በክረምቱ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የቤታቸው እድሳት ተጀምሯል። የኢዜአ ሪፖርተር በስፍራው ተገኝቶ ወይዘሮ ባሎን ባነጋገራቸው ወቅት “ሰው በሚያስፈልገኝ ጊዜ ሰዎች ሁነው የተገኙ ወገኖቼ ችግሬን ለመፍታት በአካል ተገኝተዋል፤ በጣም ደስ ብሎኛል፤ የመኖርን ተስፋ እንድሰንቅ አድርገውኛል በማለት ደስታቸውን በእንባቸው ጭምር ታጅበው ገልጸዋል። የሀመሯ እናት ቤታቸው በፍጥነት ታድሶ የሚረከቡ፣ በቀጣይም አስፈላጊው እገዛና ድጋፍ የሚደረግላቸው መሆኑን የቤቱን እድሳት ያስጀመሩት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር አረጋግጠዋል። እንደ ወይዘሮ ባሎ፤ ያሉ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖችን የማገዝና የመደገፍ ሃላፊነት አለብን ያሉት ሃላፊው፤ የመረዳዳትና የመተጋገዝ ባህል ጎልቶ እንዲቀጥል ሁላችንም የድርሻችንን ልንወጣ ይገባል ብለዋል። የቢሮው የማኔጅመንት አባላትና ሰራተኞች ለወገኖቻቸውያላቸውን አለኝታነት በተግባር በማሳየታቸውም አመስግነዋል። የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ፤ የዘንድሮ የክረምት በጎ ፈቃድ ተቋማት፣ግለሰቦች፣ወጣቶችና አዛውንቶች ሳይቀር የተሳተፉበት እና የበርካቶችን ችግር መፍታት የተቻለበት መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ማኔጅመንት አባላትና ሰራተኞች የወይዘሮ ባሎን ቤት ለማደስ በመምጣታቸው አመስግነው፤ ለሌሎች ተቋማትም አርአያ የሚሆን የመልካምነት ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ በተያዘው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ቤቶችን ጨምሮ የዞኑን ማህበረሰብ ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም በዞኑ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖችን የመደገፍና ሰው ተኮር የልማት ስራዎችን በስፋት የማከናወን ተግባር በተጠናከረ መለኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል።
የአባይ የቁጭትና የወቀሳ ጊዜ አበቃ!
Sep 9, 2025 396
የአባይ የቁጭትና የወቀሳ ጊዜ አበቃ! (በቀደሰ ተክሌ - ከሚዛን አማን) አኩርፎ ከቤት ቢወጣ ለመመለስ ሸምጋይ አጥቶ በሰው ሀገር ተንከራታች ልጓም አልባ ሆኖ የኖረው አባይ ከኢትዮጵያ አፈር፣ ማእድናትና ሌሎችንም ሃብቶች ጠርጎ በመውሰድ ለዘመናት ሲፈስ ኖሯል። ከኢትዮጵያ እምብርት በመነሳት አገራትን አቆራርጦ የሚያልፈው፣ የዓለማችን ታላቁ ወንዝ አባይ በጋና ክረምት ሳይል በመፍሰስ የብዙዎች የህይወት ምንጭ ሆኖ አሁንም ፍሰቱን ቀጥሏል። የኢትዮጵያ ልጅ የኢትዮጵያውያን አብሮነት ምሰሦ - የወንዞች ንጉሥ ታላቁ አባይ! አሁን ልጓም ተበጅቶለት በፍትሃዊነት ሁሉንም ለመጥቀም ተዘጋጅቶ የማይነጥፈው ጅረት ዘላለማዊ የመፍሰስ ሂደቱ እንደቀጠለ ነው። ኢትዮጵያውያን አመሉ ለከፋ፤ እሺ በጀ አልል ብሎ በእንቢታ ልቡን ባጸና ልጅ አብዝተው ያዝናሉ። የሀዘናቸው ጥግም በሕይወት ሳለ የሞተ ያክል በእንጉርጉሮ ሙሾ ያወርዱለታል። አባይም ይህ እጣ ፈንታ ገጥሞት "አመፀኛ ውሃ" ተብሎ በወቀሳ ተዚሞለታል። ለኢትዮጵያ ለዘመናት ሳይታዘዝ የኖረው አባይ የአዛዥ እጦት እንጂ በእምቢታ አልነበረም። በዚህ ውጣ በዚህ ግባ ባይ አጥቶ ቦዘነ። በዚህም ተራራውን እየሸሸ ቁልቁል እየተምዘገዘገ፣ ሲሻ እየጬሰ ቁልቁል ወርዶ ከዐለት ጋር እየተጋጨ መዳረሻውንና ማደሪያውን ይናፍቃል። በዚህም ቤቱን ረሳ። ወላጆቹን ትቶ ባእዳንን ብቻ ጦረ፣ ፊቱን በፍጹም ወደ ኋላ እንዳይመልስ እንደ ሎጥና ቤተሰቦቹ ተገዘተ። አባይ የባእዳንን ግዝት ከተፈጥሮ ጋር አስተባብሮ በመጠበቅ ሀገሩን ለቆ ከመውጣት ውጭ ቢደክመው የማረፍ፥ ቢመቸው የማልማት መብት ሊያገኝ አልቻለም። ይህ በኢትዮጵያ ልብ ውስጥ ቁጭት ፈጥሮ ከትውልድ ወደ ትውልድ ተሸጋገረ። ኢትዮጵያ ለታላቅ ልጇ ማረፊያ ሠርታ ጎጆ ልታወጣ ቋመጠች። ፈተናው በዛ የፖለቲካ መልክ ይዞም አቅሟን ተፈታተነ። ስደተኛው አባይን ስላሳረፉት እርሱም ስለመገባቸው የግል ሀብት አድርገው የቆጠሩት የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ጫና ፈጥረው የሀሳብ ጽንሱን ከታሪካዊና ቀጣናዊ ጠላቶች ጋር እየተባበሩ አቋረጡት። አባይን ገድቦ የመጠቀም የዘመናቱ የኢትዮጵያ መሪዎች ጉጉቱ ህልም ሆኖ ሐዘኑ ከነ ቁጭቱ ቀጠለ። እንጉርጉሮ ወቀሳ በበዛባቸው ስንኞች ቋጥሮ መዜሙን ቀጠለ። የኢትዮጵያ ዐይኖች ጀግንነት በአባይ ሲሸበብ ማየት አንገሸገሻቸው። የበይ ተመልካች መሆንና ከጓሯቸው ሞፈር አስቆርጦ መራብ አመማቸው። ኢትዮጵያዊነት ከዘመን ዘመን የማይነጥፍ፥ ልብ ለልብ የተሳሰረ ትውልድ ማንነት ማሳያ ሐውልት ነው። ትላንት ዛሬን እያቃና ነገን የሚገነባበት ሀገራዊ ራእይ ያላቸው መሪዎች ትስስር በአባይ ሲንጸባረቅ ይስተዋላል። ከ1929 እስከ 1950ቹ ያለው የአባይ ፖለቲካ ጉዳይ በብዙ ድርድሮችና ስምምነቶች ታጀበ። የጫና ፈተናው አየለና ገንብቶ የመጠቀም ጥንስስን ለቀጣይ ትውልድ እንዲሸጋገር አደረገ። ያኔ ነገን የተመለከተ ዐይን "ልጆቻችን ይሠሩታል" የሚል ቃል ሰጠና ኢትዮጵያ ልጆቿን በተስፋ ተጠባበቀች። ዘመን አለፈ ትውልድ ተተካ ልጆችም ተወለዱና የተስፋ ቀጠሮ ደረሰ ወርሃ መጋቢት 2003 ዓ/ም። በዚህ ቀን የታላቁ ኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ዜና በቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ተበሰረ። ኢትዮጵያ እልል አለች፤ "እንጉርጉሮ ይብቃ" ተባለ በዜማ በዝማሬ አባይ ተሞገሰ። የአባይ የወቀሳ ጊዜ ተጠናቀቀ- የቁጭት ጊዜ አብቅቶ የስኬትና ማንሰራራት ጊዜ መጣ። ለግድቡ የ14 ዓመታት የግንባታ ሂደት ከአንድ ብር ጀምሮ አስተዋጽኦ ያደረጉ፣ በእውቀትና በጉልበት የተጉ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ የደስታ ቀንም እውን ሆነ። በጉባ ሰማይ ስር አዲስ ክስተት፣ አዲስ ምዕራፍ፣ አዲስ ስም ተተከለ። አባይ ከሚል ነጠላ ስም ወደ "ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ" ተሻገረ። የድግቡ ሃይቅም "ንጋት" የሚል መጠሪያ ወጥቶለት ለኢትዮጵያ የንጋት ጸሃይ እየወጣች መሆኑን ለሁላችንም ብስራት ሆነ። "እንኳንም ጀመርን፣ እንኳንም በር ተከተፈተልን" እንጂ ያሉት ልበ ኩሩና ክንደ ብርቱ ኢትዮጵያውያን ጫናዎችን በአይበገሬነት መንፈስ ድባቅ እየመቱ ጉዞ ወደ ፊት ቀጠሉ። ወደ ተግባር ገብተው "ሕይወታችንንም ቢሆን ለአባይ አንሰስትም" አሉ። ግድቡን እንሠራለን ብለው የጀመሩት ኢትዮጵያውያን ናቸው። ከነ አባባላቸው "የነብር ጭራን አይያዙ፥ ከያዙም አይለቁ" ነውና ሥራውን ስለጀመሩት የአባይ ግድብ ጉዳይ ቀዳሚ አጀንዳቸውና ደም ስራቸው ሆኖ ቀጠለ። እንደ ዐይን ብሌናቸው ያዩ፣ ይጠብቁት እና ይሳሱለት ጀመር። የአልሸነፍ ባይነት ወኔን ከጀግንነት ጋር አጣምረው የያዙ ኢትዮጵያውያን የጠላት ነቀፋና ፕሮጀክቱን የማኮላሸት ሴራን እንደ ድር አብረው ተከላከሉ። የ"እንችላለን" ትርክትን በተግባር ነፍስ እየዘሩ እጅ ለእጅ ተያይዘው ጉዟቸውን ከሕዳሴ ጋር ቀጠሉ። በጉባ ምድር ላይ የአንድነታቸውን ቋሚ ሐውልትም ተከሉ። ኢትዮጵያውን ከአድዋ ጦርነት ወዲህ የአንድ ቃል ተናጋሪ የአንድ ልብ መካሪ ሆነው የተከሰቱበትና በአንድ የተመሙበት ትልቁ የታሪክ አሻራ አባይ በሕዳሴ ሆነ። የተማሪ ቦርሳ፣ የእናቶች መቀነት፣ የአረጋውያን የጡረታ ደብተር፣ የአርሶ አደሮች ጎተራ፣ የአርብቶ አደሮች በረት፣ የመንግሥት ሠራተኛው ፔሮል፣ የነጋዴው ኪስ እና የዳያስፖራ ዋሌት ሳይቀር በአባይ ላይ አሻራ አለው። የሕዳሴው ግድብ ውዝግብ ኢትዮጵያ ራሷን በዓለም መድረክ ከፍ አድርጋ ያሳየችበት ትልቅ አጋጣሚ ነው። ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የደረሰውን ውሃ አይሞላ ክስ በብስለት መክታ እውነትን ለዓለም ሕዝብ አስገንዝባለች። በዚህም የዓለም አቀፍ ሕግ አዋቂነቷንና አክባሪነቷን፣ የጋራ ተጠቃሚነት ፍላጎቷንና ለሰላም ያላትን አቋም ቁልጭ አድርጋ አረጋግጣለች። ድርድሮችን በድል የሚቋጩ ልጆቿ ደግሞ ኢትዮጵያውያን በሁሉም ዘርፍ ብቁ የመሆናቸው ነጸብራቅ ሆነው ተከሰቱ። ዘርፈ ብዙ የዲፕሎማሲ ሥራው ከማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚ እስከ ጉምቱ አምባሳደሮች በተናበበ መልኩ ብቅ ብሎ አጀብ አስብሏል። ድርድሩ በመስመሩ፣ የዲፕሎማሲ ሥራው በሜዳው ፖለቲካ እና ሌላው የሀገር ጉዳይ በየፈርጁ እየቀጠለ የሕዳሴው ግድብም ለደቂቃ እንኳ ሳይቆም ይሠራ ነበር። ይህ የመብቃት፣ የማደግ፣ በጥበብ የመበልጸግ፣ በሀሳብና አቅም የመብሰል ሀገራዊ ማሳያ ነው። ለብዙ የአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ የሚሆን አሻጋሪ የተግባር ልምምድ መሆኑም አያሻማም። ለዚህ ግድብ ስኬት ደግሞ የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን መሪ ሆነው ብቅ ያሉትን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶር) ማንሳት ግድ ይላል። አዛዥ አጥቶ ቦዝኖ የነበረውን ጊዜ ለመካስ ና ብሎ የሚጣራውን አዛዥ "አቤት" ብሎ ትዕዛዝ ለመቀበል አባይ አላቅማማም። አሁን በሙሉ ልቡ ወደ ጫጉላ ቤቱ ገብቷል። የመስከረሙ ሙሽራ የቤት ሀብት ዘርፎ ለባዕድ አሳልፎ ከመስጠት ተቆጠበ። የበረሃው ሀሩር ሳይመታው በሀገሩ እፎይ ብሎ ብርሃንም ምግብም፣ ሀብትም ክብርም መሆን ጀመረና የኢትዮጵያን ክብር ዳግም ከፍ አደረገ። ሰው ተፈጥሮን ሲያዝ እሺ ይላል፥ ዝም ካሉት በራሱ ፍላጎት ይሔዳል። ይህ ተፈጥሯዊ የአባይ ግብር ተቀይሮ በሰዎች መታዘዝ ጀመረ። አፈርና ውሃ ማስቀረት ብቻ ሳይሆን ግዙፍ የብርሃን ምንጭ ሆኖ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ብርሃን መሆን ጀምሯል። በሕዳሴ ግድብ ታዞ ፊቱን ወደ ልማት ሥራ ያዞረው አባይ ያለፈውን ለመካስ ብዙ ጸጋዎችን ይዞ ተከሰቷል። የዓሳ ምርት፣ ግዙፍ ሀይቅ ከደሴቶች ጋር አንጣሎ በመያዝ የኢኮ ቱሪዝም ዘርፍ መሪ ሊሆን ቆርጦ ተነስቷል። አብሮ የመልማት የኢትዮጵያ ጽኑ ፍላጎት በወለደው እሳቤ ህዳሴ ግድብ የጎረቤት አገራት ሃብት ጭምር በመሆን ለማገልገል ተዘጋጅቷል። አባይ ሆይ ስምህ ከወቀሳ ወጥቶ በሙገሳ ስለተተካ እንኳን ደስ አለህ! እናቴ ሆይ የተፈታው መቀነትሽ ሀይል ስላመነጨ ለልጆችሽ ሀብት አውርሰሻልና ደስ ይበልሽ። ሀገሬ የብርሃን ዘመን ስለፈነጠቀብሽ እንኳን ደስ አለሽ! ሰላምና ፍቅር ለሁላችን ይሁን።
የትውልዱ ድል፤ የብርሃን ጅረት
Sep 8, 2025 321
አቶ ዲሮ ቱፋና ዓለሚ በዳዳ በምዕራብ ሸዋ ዞን ወልምራ ወረዳ ነዋሪ ናቸው። አካባቢያቸው ለአዲስ አበባ ከተማ ቅርብ ቢሆንም እስካሁን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ማግኘት አለመቻላቸውን ያነሳሉ። የኤሌክትሪክ ሃይል ሽፋን ባለመዳረሱ ምክንያት ኑሯቸው አስቸጋሪ ሆኖባቸዋል፤ ማገዶ መጠቀማቸው ደግሞ ለጤናቸው ተግዳሮት እየሆነባቸው መጥቷል። እነርሱ እንደሚሉት የማገዶ እንጨት ለማምጣት ረጅም ርቀት በመጓዝ ለእንግልት ተዳርገዋል። የቤንች ሸኮ ዞን ነዋሪዋ አበበች ደጎሽም በአካባቢያቸው የኤሌክትሪክ ሃይል ባለመኖሩ ምክንያት ሕይወታቸውን ፈታኝ አድርጎታል። ልጃቸው ለማጥናት የሻማና ኩራዝ መብራት ለመጠቀም ትገደዳለች። በዚህ ላይ ምግብ ለማብሰል ከሰል መጠቀማቸው በጤናቸው ላይ ችግር እየፈጠረ መጥቷል፤ በተለይ በመተንፈሻ አካላቸው ላይ ያጋጠማቸው እክል ለሀሳብ ዳርጓቸዋል። በምዕራብ ሸዋ ዞንና በቤንች ሸኮ ዞን ያሉት ሁለቱን ቤተሰቦች ተስፋ ያስተሳስራቸዋል። ለኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎታቸው ምላሽ ለማግኘት ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሚመነጨውን ሃይል በተስፋ ይጠባበቃሉ። በመላው ኢትዮጵያውያን ቁርጠኝነት፣ የገንዘብ መዋጮና የተቀናጀ ትብብር እውን የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ይዞ እየመጣ ካለው የ5 ሺ 150 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል ተቋዳሽ እንደሚሆኑ ይተማመናሉ። መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መሠረተ ድንጋይ በቤንሻንጉል ጉምዝ ጉባ ወረዳ ከተቀመጠ ከዓመታት በኋላ መጠናቀቁን ተከትሎ እንደ አቶ ዲሮ ቱፋና ዓለሚ በዳዳ ያሉ ተስፋቸው ለምልሟል። ከሚያመነጨው የኤሌክትሪክ ሃይል ተቋድሰው መብራት በማግኘት ኑሯቸውን የሚያሻሻሉበትን መንገድ በተስፋ ይጠባበቃሉ። ለዚህም ነው ባለፉት ዓመታት ኢትዮጵያዊያን በዓባይ ወንዝ ላይ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ገንዘባቸውን፣ እውቀታቸውንና ጉልበታቸውን በማዋጣት የግድቡን ግንባታ በቁርጠኝነት ያካሄዱት። መነሻውን ከኢትዮጵያ አድርጎ 6 ሺ 696 ኪሎ ሜትር ርዝመት የሚጓዘው የዓባይ ወንዝ ከዓለማችን ረጃጅም ወንዞች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት ተጠቃሽ ነው። ረጅም ኪሎ ሜትር ለሚጓዘው የዓባይ ወንዝ 86 በመቶ የውሃ ድርሻ የምትሸፍነው ደግሞ ኢትዮጵያ ናት። ኢትዮጵያ የገነባችው ታላቁ የህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ለአቶ ዲሮና መሰሎቻቸው ኑሯቸውን ለማቃለል የሚያስችል የመብራት ሃይል ከማቅረብ ባሻገር ለጎረቤት አገራት የኤሌክትሪክ ሃይል በመሸጥ ትስስር ለመፍጠር የሚያስችል አቅም እንደሚሆን ነው ባለሙያዎች የሚገልጹት። ይህ ደግሞ የተፋሰሱ አገሮች በኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት መተሳሰር የሚያስችል፣ በጋራ በመልማት ዕድገታቸውን ለማፋጠን እድል የሚከፍት መሆኑን ነው ባለሙያዎች የሚስማሙት። ይህ ግን በቀላሉ የተገኘ ዕድል ላለመሆኑ ያለፉት ዓመታት ተግዳሮቶች ተጠቃሽ መሆናቸው አጽንኦት የሚሰጠው ጉዳይ ነው። የቀድሞው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የተደራዳሪ ቡድን አባልና የውሃ ሃብት አስተዳደር፣ ወሰን ተሻጋሪ ወንዞችና የሃይድሮ ዲፕሎማሲ አማካሪ ፈቅ አሕመድ ነጋሽ፤ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እንዲጓተት፣ መንግስትና ህዝብ ተስፋ ቆርጠው እንዲተውት ብዙ ሙከራዎች ቢደረጉም በኢትዮጵያውያን የጋራ ጥረት ማጠናቀቅ መቻሉን ያነሳሉ። የዓለም አቀፍ የውኃ ሕግ ባለሙያው ከበደ ገርባ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያን ከዓባይ ውሃ ለመነጠል ዘርፈ ብዙ አደናቃፊ የዲፕሎማሲ ስራዎች ቢሰሩም ግንባታውን ማስተጓጎል ያለመቻሉን ነው አጽንኦት የሰጡት። የቀድሞው የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትርና በአሜሪካ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ስለሺ በቀለ (ዶ/ር) በአንድ ወቅት ግንባታው እንዳይጠናቀቅ ከውጭ ሃይሎች ባለፈ በአገር ውስጥ የተለያዩ ተግዳሮቶች ገጥመውት እንደነበር መግለጻቸውን እዚህ ላይ መጥቀስ ይቻላል። በኢትዮጵያ ለውጥ ከመጣ በኋላ መንግስት ግድቡ ላይ ከፍተኛ ርብርብ በማድረግ በተሻለ ፍጥነትና ጥራት ተገንብቶ እንዲያልቅና ለታለመለት ዓላማ እንዲውል መስራቱ ተገልጿል። ኢትዮጵያ የተፋሰሱ አገሮች የዓባይ ወንዝን በፍትሃዊነት የመጠቀም አስፈላጊነትን የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በመጀመር በተግባር የተገለጠ እርምጃ መውሰዷ በአካባቢው አገሮች ላይ ተስፋን አጭሯል። ለዚህም ነው የናይል ተፋሰስ አገራት በዓባይ ውሃ አጠቃቀም ላይ ፍትሃዊና ምክንያታዊ አጠቃቀም እሳቤ እንዲኖራቸው የናይል ተፋሰስ አገራት የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ሰነድ (CFA) እ.አ.አ በ2010 ተዘጋጅቶ አገሮች እንዲስማሙ እድል የተሰጠው። ይህም ለዓባይ ውሃ ምንም ድርሻ የሌላቸው የታችኞቹ ተፋሰስ አገራት እ.አ.አ በ1929 እና በ1959 የዓባይን ውሃ በብቸኝነት ለመጠቀም የተፈረሙትን የቅኝ ግዛት ውሎች ውድቅ የሚያደርግና በተፋሰሱ አገራት መካከል አዲስ የትብብር ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑን የዘርፉ ምሁራን ይገልጻሉ። የናይል ተፋሰስ አገራት የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ሰነድ እ.አ.አ በ2010 ለፊርማ ክፍት ከሆነ በኋላ ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ታንዛንያና ዩጋንዳ፣ ደቡብ ሱዳንና ብሩንዲ ፈርመዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የውሃ ሃብት መምህርና ተመራማሪ ኤርሚያስ ተፈሪ (ዶ/ር) እንደሚሉት፤ የማዕቀፍ ስምምነቱን ስድስቱ አገራት ሰነዱን በፓርላማቸው ካጸደቁ የናይል ኮሚሽን ማቋቋም ይችላሉ። እንደ ቀድሞው የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የተደራዳሪ ቡድን አባልና የውሃ ሃብት አስተዳደር ፣ወሰን ተሻጋሪ ወንዞችና የሃይድሮ ዲፕሎማሲ አማካሪው ፈቅ አሕመድ ነጋሽ፤ በአሁን ወቅት ስድስቱ አገራት ስምምነቱን መፈረማቸውን ተከትሎ የናይል ተፋሰስ ኮሚሽን ተቋቁሟል። የውሃ ሃብት መምህርና ተመራማሪ ኤርሚያስ ተፈሪ (ዶ/ር) እንደሚሉት፤ ከዓባይ ተፋሰስ አገራት መካከል ግብጽና ሱዳን የኤሌክትሪክ ሃይል ሽፋናቸው ከፍተኛ በመሆኑ ከኢትዮጵያ ጋር ሊነጻጸር የማይችል መሆኑን ነው የሚያነሱት። ይህም በጤና፣ በትምህርት እና በኑሮ ዘይቤ ላይ የሚያስከትለው አሉታዊ ተጽዕኖ ከፍተኛ ነው ይላሉ። ይህን ችግር ለማቃለልና ብርሃንን ለሁሉም ለማዳረስ ታላላቅ ፕሮጀክቶች ግድ ይላሉ ብለዋል። ኢትዮጵያውያን በ''እንችላለን'' መንፈስ ከተማሪ እስከ ሰራተኛ፣ ከጡረተኛ እስከ ወታደር፣ ከቤት እመቤት እስከ ባለሃብት ሁሉም በደረጃውና በአቅሙ በገንዘብ በሀሳብና በጉልበት ለመሳተፍ ቁርጠኛ አቋም በመያዝ የግድቡን ግንባታ እውን ለማድረግ ተረባርበዋል። የታላቁ ህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ዋና ስራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር)፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን በራስ አቅም በራስ ዕውቀትና ሀብት የማይቻል የሚመስለውን ችለው ያሳዩበት አኩሪ ታሪክ ነው ይላሉ። እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ መጻዒ ዕድሉን የተሻለ ለማድረግ ከዕውቀቱ፣ ከገንዘቡና ከጉልበቱ አዋጥቶ እውን ያደረገው የዳግማዊ ዓድዋ ድል መሆኑን የሚናገሩት ደግሞ የጥንታዊ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ፕሬዚዳንት ልጅ ዳንኤል ጆቴ ናቸው። የዓለም አቀፍ የውኃ ሕግ ባለሙያው ከበደ ገርባ (ዶ/ር) እንደሚሉት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በርካታ ውጣ ውረዶችን አልፎ መጠናቀቁ የትውልዱ ድል ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሁለተኛው ዙር የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ውሃ ሙሌት ሥነ-ሥርዓት ላይ በታሪክ ውስጥ ማለፍ ዕድል ፣ታሪክ መስራት ደግሞ ድል ነው ይላሉ። የታላቁ ህዳሴ ግድብ የአሁኑ ትውልድ ዕድልና ድል መሆኑንም ነው ያነሱት።
በቤተሰብ የተቀረፀው የእህትማማቾቹ የሃገር ፍቅር ስሜት
Sep 2, 2025 619
በቤተሰብ የተቀረፀው የእህትማማቾቹ የሃገር ፍቅር ስሜት... ኢትዮጵያ በየዘመናቱ በገጠሟት ችግሮች ሁሉ የበርካታ ጀግኖች መፍለቂያ መሆኗን ያረጋገጠች ሀገር ናት፤ ይህም በአለም አደባባይ ነጻነቷ ተከብሮ፣ ታፍራና ተከብራ እንድትኖር ምክንያት ሆኗል። ኢትዮጵያ በጀግኖች መስዋእትነት ሉአላዊነቷን አስጠብቃ ኖራለች፤ ወደፊትም ነጻነቷ የተከበረ፣ በኢኮኖሚ የበለጸገች፣ ዜጎች ኮርተው የሚኖሩባት ጠንካራ ሀገር ሆና ለመቀጠል በላቀ ትጋት ላይ የምትገኝ ሃገር ናት። ይህ ጽሁፍ በላቀ የሃገር ፍቅር ስሜት ተነሳስተው፤ ለግዳጅ ተዘጋጅተው የራሳቸውን የጀግንነት ህልምና ትልም እውን ለማድረግ በብር ሸለቆ መሰረታዊ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት ሰልጥነው በተመረቁ እህትማማቾች ላይ ያተኩራል። ውልደትና ዕድገታቸው በአዲስ አበባ የሆኑት እህትማማቾቹ ስመኝ ወርዶፋ እና ቃልኪዳን ወርዶፋ በብር ሸለቆ መሰረታዊ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት በመሰረታዊ ወታደርነት ሰልጥነው ተመርቀዋል። ከቤተሰባቸው የወረሱት ከፍተኛ የሃገር ፍቅር ከህጻንነታቸው ጀምሮ በልባቸው እየተብላላ፣ በአዕምሯቸው እየተብሰለሰለና መዳረሻውን እየፈለገ መኖሩን አስረግጠው በኩራት ይናገራሉ። ለሃገር ፍቅር ስሜቱ ምንጭና ጥንስሱም መኖር፣ ማጌጥ፣ መደሰት፣ ማዘን… የሚቻለው በሀገር ላይ ነው፤ ሀገር ስትኖር ሁሉም ህልምና ትልም ይሳካል ተብሎ እየተነገራቸው ማደጋቸው ነው። እህትማማቾቹ ለዘመናት ህልማቸው የሆነውና በልባቸው እየሰረጸ በውስጣቸው እየታገላቸው የሚገኘውን የሃገር ፍቅር ስሜት እንዴት፣ መቼና የት እውን እንደሚያደርጉት ማሰላሰል ከጀመሩ ከራርመዋል። ይህንን ህልማቸውን እውን የሚያደርጉበትን መንገድ በማፈላለግ ላይ እያሉ የሃገር መከላከያ ሰራዊት ማስታወቂያ ማውጣቱን ተመለከትን ይላሉ። ይህም የህልምና ትልም ታሪክ በብር ሸለቆ መሰረታዊ ወታደር ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት በመሰልጠን ተመራቂ ሆነው ተገኝተዋል። መሰረታዊ ወታደር ስመኝ ወርዶፋ ከኢዜአ ጋር በነበራት ቆይታ፤ በራሳችን ሙሉ ፈቃድ ወደዚህ ታላቅ ተቋም መቀላቀላችን እኔም ሆንኩ እህቴ በጣም ደስተኛ ነን ስትል በልበ ሙሉነት ገልጻለች። የሃገር መከላከያ ሰራዊት ያወጣውን ማስታወቂያ እንዳየሁ "ለታናሽ እህቴ ቃልኪዳን የዘመናት ህልማችን እውን የምናደርግበት ታላቅ ብስራት ነው ብዬ ነገርኳት" የምትለው ስመኝ፤ በዚህም ውጥናችንን የምንተገብርበትን መንገድ ለመጀመር አላቅማማንም ብላለች። ምንም እንኳ በልባችን ፀንቶ ከአካላችን ጋር እያደገ የመጣው የላቀ የሀገር ፍቅር ስሜት ሁለታችንንም ገፋፍቶን በጉዳዩ ላይ መክረን እድሉን መጠቀም እንዳለብን መግባባት ላይ ሊያደርሰን ችሏል ትላለች መሰረታዊ ወታደር ስመኝ። በፈቃዳችን ተመዝግበን ወደ ብር ሸለቆ በመምጣት የስነ ልቦና፣ የቴክኒክ፣ የአካል ብቃትና የውጊያ ስልቶችን በተግባርና በንድፈ ሃሳብ ተማርን፤ በዚህም ብዙ ለውጦችን አግኝተንበታል ስትል ገልጻለች። እኔና እህቴ ወደዚህ ከመምጣታችን በፊት ተነጋግረን፣ ተመካክረንና ወስነን ነው የመጣነው ያለችው ስመኝ ፤ አሁን ላይ ስልጠናውን በብቃት አጠናቀን ለቀጣይ ግዳጅ ዝግጁ በመሆናችን ደስተኛ ነን ብላለች። የዘመናዊ መከላከያ ሰራዊት መርህን በመከተልና የሚሰጠንን ተልእኮ በላቀ ብቃት በመፈጸም ሀገራችንና ህዝባችንን ለማገልገል ዝግጁ ነን ስትል ተናግራለች። ሁለታችንም ብር ሸለቆ መሰልጠናችን እየተረዳዳን፣ እየተደጋገፍን፣ እየተመካከርን… ስልጠናውን በከፍተኛ ብቃት ለማጠናቀቅ አስችሎናል፤ ብቸኝነትን በማስወገድ ፈጥነን ተላምደን በሙሉ ልብ ስልጠናውን ለመከታተል አግዞናል ብላለች። የስመኝ ታናሽ እህት የሆነችው መሰረታዊ ወታደር ቃልኪዳን ወርዶፋ በበኩሏ፤ የመከላከያ ሰራዊትን መቀላቀሌ ከልጅነቴ ጀምሮ በውስጤ የኖረውን ፍላጎትና ህልም እንዳሳካ አስችሎኛል ስትል ገልጻለች። እኔና እህቴ ውስጣችን የነበረውን የሀገር ፍቅር የምንገልጽበት ተቋም ውስጥ በመግባታችን ደስታችን ወደር የለውም ያለችው ቃልኪዳን፤ ከራሳችን በፊት ቅድሚያ ለሃገርና ለሕዝብ የሚለውን የመከላከያ መርህ ለመተግበር ቆርጠን ተነስተናል ብላለች። የሀገር ፍቅር ስሜታችን የመነጨው ከቤተሰብ ነው፤ የመሰረታዊ የውትድርና ስልጠና ወስደን መመረቃችን ትልማችንን እውን ለማድረግ እድል ይፈጥርልናል ብላለች። “የነብርን ጅራት አይዙም፤ ከያዙም አይለቁም” እንደሚባለው ካሁን በኋላ ያገኘነውን እውቀትና ክህሎት ተጠቅመን የሚሰጠንን ተልእኮ በጀግንነት ለመወጣት ቁርጠኛ ነኝ ስትል አንስታለች ቃልኪዳን ። የመከላከያ ሰራዊቱን ስቀላቀል ሀገሬን ለማገልገል ነው፤ የሃገሬንና የሕዝቤን ክብር ለማስጠበቅ እኔ አስፈላጊውን መስዋዕትነት ለመክፈል ተዘጋጅቻለሁ ስትል ገልጻለች። የዘመናዊ ወታደር ስብእናን በመላበስ በሀገራችን ዴሞክራሲ ስር እንዲሰድ፣ የተጀመረው ልማት ዳር እንዲደርስና የሕዝብ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ የድርሻዋን ለመወጣት ቁርጠኛ መሆኗን ተናግራለች። ለዚህም በምትሰማራበት የግዳጅ ቀጠና ሁሉ የሚሰጣትን ተልእኮ ሁሉ በላቀ ተነሳሽነት በመፈጸምና ለተደማሪ ድል በመዘጋጀት ትልሟን በመተግበርና ዳር በማድረስ አሻራዋን ለማስቀመጥ እንደምትተጋም አረጋግጣለች። የእነዚህን ብርቅዬ የሀገር ጀግኖች ታሪክ ለሕዝብ እንዲደርስ ለአብነት ተነሱ እንጂ ሶስት ወንድማማቾች ሆነው የገቡና ሌሎች ታሪኮች ያሏቸው ጀግኖች የመሰረታዊ ውትድርና ተመራቂዎች መኖራቸውን መመልከት ይቻላል። ይህም ኢትዮጵያ የበርካታ ጀግኖች መፍለቂያ ሀገር መሆኗን የሚያሳይ እና ጀግንነት ደግሞ በግለሰብ፣ በቤተሰብ፣ በማህበረሰብና በድምር ውጤት በሀገር የሚገለጥ ሲሆን፤ የእህትማማቾቹ ታሪክ ከቤተሰብ የተገኙ ጀግኖች ናቸው። የጀግንነት ዋናው ምእራፍ ፍላጎት፣ ተነሳሽነት፣ ቁርጠኝትና ዝግጁነት በመሆኑ ሁለቱ ባለታሪኮቻችን እነዚህን ጉዳዮች አሟልተው በግንባር ለሚመዘገበው ድል አኩሪ ተጋድሎ ለመፈጸም የተዘጋጁ ናቸው።
የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል አብዮት
Aug 27, 2025 758
በሙሴ መለስ/ኢዜአ ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ የአረንጓዴ ኃይል ዋንኛ ማዕከል በመሆን ላይ ትገኛለች። የተፈጥሮ ውበቷን ከኢኖቬሽን ጋር በማስተሳሰር የአየር ንብረትን የማይበክሉ የተለያዩ የታዳሽ ኃይል አማራጮችን እየተጠቀመች ይገኛል። አዲስ አበባ ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ለማስተናገድ ዝግጅቷን አጠናቃ እንግዶቿን እየተጠባበቀች ነው። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ስራ በጉባኤው ከምታቀርባቸው ተሞክሮዎች መካከል ይጠቀሳል። ኢትዮጵያ ከውሃ፣ ከፀሐይ፣ ከነፋስ፣ ከእንፋሎት ሃይል፣ ባዮማስ ከእንስሳትና እጽዋቶች ተረፈ-ምርት ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅም አላት። ይህም የሚያሳየው አብዛኛውን የኤሌክትሪክ ኃይል የምታገኘው ከታዳሽ የኃይል ምንጮች መሆኑን ነው። ኢትዮጵያ ከጂኦተርማል 10 ሺህ ሜጋ ዋት ከንፋስ ኃይል ደግሞ 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሀይል የማመንጨት እምቅ አቅም አላት። ግንባታው የተጠናቀቀው እና 5 ሺህ 200 ሜጋ ዋት የሚያመነጨው የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብም ከብክለት ነጻ የኃይል ምንጭ ከመሆን ባለፈ ለሀገሪቷ ኢኮኖሚ አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል። መንግስት የሀገሪቱን የኃይል እጥረት ለመቅረፍ በዋና ዋናዎቹ የወንዞች ተፋሰሶች የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ፕሮጀክቶችን በማልማት ላይ ይገኛል። በ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅዷ ኢትዮጵያ የምታመነጨውን የኃይል መጠን አሁን ካለበት 4 ሺህ 818 ሜጋ ዋት ወደ 17 ሺህ ሜጋ ዋት ለማሳደግ ግብ ተቀምጧል። የተሻሻለው የኢነርጂ ፖሊሲዋም ሀገራዊ፣ ቀጣናዊና ዓለም አቀፍ ነባራዊ ዕውነታ መሰረት ያደረገ እና ጎረቤት ሀገራትን በኃይል መሰረተ ልማት ለማስተሳሰር ያለመ ነው። ይህንንም እውን ለማድረግ በመንግስት ከሚለሙት የኃይል ምንጮች በተጨማሪ በግሉ ዘርፍ ኃይል ተመርቶ የኃይል አቅርቦቱ እንዲሻሻልና ዘላቂ እንዲሆን አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡ ይህንንም እውን ለማድረግ በ2009 ዓ.ም በገንዘብ ሚኒስቴር ስር የመንግስትና የግሉ ዘርፍ አጋርነት ፕሮጀክት በአዋጅ ቁጥር 1076/2018 ተመስርቷል። በዚህ የመንግስትና የግሉ ዘርፍ አጋርነት ስምንት የፀሐይ ኃይል፣ አምስት የሃይድሮ ኤሌክትሪክ እና አምስት የንፋስ ኃይል ፕሮጀክቶችን ለማልማት እየተሰራ ይገኛል። ከስምንቱ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች እስከ 750 ሜጋ ዋት ኃይል ለማግኘት መታቀዱን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መረጃ ያመለክታል። ጋድ 1 እና 2፣ ዲቼቶ፣ ወራንሶ፣ ሁመራ፣ ወለንጪቲ፣ መቀሌ፣ ሁርሶ እና መተማ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶቹ ናቸው። አዳማ አንድ፣ አዳማ ሁለት፣ አይሻ ሁለት እና አሸጎዳ ከንፋስ ኃይል ፕሮጀክቶቹ መካከል ይጠቀሳሉ። የእንፋሎት (ጂኦተርማል) ኃይልን በተመለከተም በመንግስትና የግሉ ዘርፍ አጋርነት ፕሮጀክት ኮርቤቲ ከሚባል የግል አልሚ ጋር መንግስት ተዋውሎ ድርጅቱ የሚያመርተውን 150 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ለኢትዮጵያ ለማቅረብ እየሰራ ይገኛል። በአጠቃላይ በተለያዩ የኢነርጂ አማራጮች የኢትዮጵያን የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነት ሽፋንን 54 በመቶ ማድረስ መቻሉን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። በብሔራዊ ኤሌክትሪፊኬሽን ፕሮግራም አማካኝነት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2030 65 በመቶ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከብሔራዊ የኃይል ቋት እንዲሁም ቀሪው 35 በመቶ ከኃይል ቋት ውጭ ባሉ ቴክኖሎጂዎች ተደራሽ የማድረግ እቅድ ተይዟል። ኢትዮጵያ ከራሷ አልፋ ለምስራቅ አፍሪካ ሀገራት እያቀረበች ያለው አረንጓዴ የኃይል አማራጭ የአየር ንብረት ተጽእኖን ለመከላከል እና ከባቢ አየርን ለመጠበቅ ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው። የተሻሻለው የኢነርጂ ፖሊሲዋም ሀገራዊ፣ ቀጣናዊና ዓለም አቀፍ ነባራዊ ዕውነታ መሰረት ያደረገ እና ጎረቤት ሀገራትን በኃይል መሰረተ ልማት ለማስተሳሰር ያለመ ነው። በርግጥ ከሕዳሴው ግድብ ባሻገር ሌላው ከአፍሪካ ግዙፍ ፕሮጀክቶች አንዱ የሆነው የኮይሻ ኃይል ማመንጫም ለቀጣናዊ ትስስር መፋጠን ሌላው እድል ነው። በጥቅሉ ኢትዮጵያ ለጎረቤት አገራት የምታቀርበው የኤሌክትሪክ ኃይል የሀገራት ኢኮኖሚ ትብብር የሚያጠናክር እና የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት የማስተሳሰር ጽኑ ፍላጎት ማሳያ ነው። በተጨማሪም በቀጣናው ዘላቂ የኤሌክትሪክ ገበያ ልማትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ክፍለ አሕጉራዊ ጥረት ነው። ጥረቱ የምሥራቅ አፍሪካ የሃይል ቋት (The Eastern Africa Power Pool-EAPP) በቀጣናው ሀገራት መካከል ድንበር ተሻጋሪ የሃይል ንግድ እና የሃይል መስመር ትስስርን ለማሳለጥ እኤአ በ2005 የተቋቋመ ተቋም ግብ እውን ከማድረግ ባለፈ አሕጉራዊ ምጣኔ ሃብታዊ ትስስርን ያፋጥናል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኢነርጂ አብዮት የአየር ንብረት ለውጥ የመከላከል ስራ እና የደን ልማትን የሚያግዝ ነው። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ እየተቃረበ ባለበት ወቅት ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኃይል አሻራውን ለአፍሪካ ለማሳየት ተዘጋጅታለች። አረንጓዴ የኃይል አማራጮች ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት የማይበገር ኢኮኖሚ መገንቢያ ዋና ምሰሶዎች መካከል ይጠቀሳል።
የኢትዮጵያ የካርቦን ገበያ፤ፍትሃዊ የአየር ንብረት ፋይናንስ አቅርቦት ማግኛ አማራጭ ---
Aug 26, 2025 577
ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል። “ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፤ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" የጉባኤው መሪ ሀሳብ ነው። ከጉባኤው አጀንዳዎች መካከል የአፍሪካ የካርቦን ሽያጭ ይገኝበታል። የካርቦን ንግድ ማለት የካርቦን ዳይኦክሳይድ እና ሌሎች የአየር ንብረት ለውጥን የሚያስከትሉ ጋዞችን ልቀትን ለመቆጣጠር የሚደረግ የገበያ ዘዴ ነው። ልክ እንደ ሌሎች ምርቶች ሁሉ የካርቦን ልቀትን የመገበያያ ዕቃ አድርጎ ይቆጥረዋል። መንግስታት ወይም ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ኩባንያዎች ወይም ተቋማት ሊለቁት የሚችሉትን ከፍተኛውን የካርቦን መጠን ይወስናሉ።ይህ መጠን “የልቀት ጣሪያ” (Emission Cap) ይባላል። ከዚያም እያንዳንዱ ኩባንያ ይህን ያህል ካርቦን የመልቀቅ “ፈቃድ” ወይም “ክሬዲት” (Credit) ይሰጠዋል። ካርቦን ክሬዲት፦ ኩባንያዎች እንደ ደን ልማት ወይም የታዳሽ ኃይልን በመሳሰሉ ፕሮጀክቶች ላይ ኢንቨስት በማድረግ ብድር የሚያገኙበት ስርአት ነው። የካርቦን ንግድ ሀገራት፣ኩባንያዎች እና ግለሰቦች በተገዢነት እና በፈቃደኝነት ላይ ተመስርተው የሚያከናወኑት ነው። አፍሪካ በዓለም ደረጃ ወደ ከባቢ አየር በሚለቀቀው በካይ ጋዝ ልህቀት ከአራት በመቶ ያነሰ ድርሻ ቢኖራትም የአየር ንብረት ለውጥ ከፍተኛ ዳፋ ተሸካሚ አህጉር ሆናለች። የካርቦን ገበያ ለአፍሪካ ሀገራት የአየር ንብረት ፋይናንስ እንዲያገኙ ከማድረግ ባለፈ ለስራ እድል እና ለብሄራዊ አየር ንብረት ለውጥ ማጣጣሚያ እቅዶች ትግበራ የበኩሉን ሚና እየተጫወተ ይገኛል። የአፍሪካ ሀገራት በ2015 ዓ.ም በግብጽ ሻርም አል ሼክ በተካሄደው 27ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንበረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ-27) የአፍሪካ ካርቦን ገበያ ኢኒሼቲቭ ይፋ አድርገዋል። በኢኒሼቲቩ አማካኝነት አፍሪካ በዓመቱ በ300 ሚሊዮን የካርቦን ክሬዲት ስድስት ቢሊዮን ዶላር ገቢ ለማግኘት አቅዳለች። እ.አ.አ በ2030 በካርቦን ንግድ ለ30 ሚሊዮን ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ውጥን ተይዟል። የካርቦን ገበያ በአፍሪካ ሀገራት ተስፋ ሰጪ እድገት እያሳየ ይገኛል። ኢትዮጵያን ጨምሮ ኬንያ፣ ጋና፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሩዋንዳ እና ሴኔጋል የካርቦን ገበያ የአሰራር ማዕቀፎችና ግቦች አዘጋጅተው እየሰሩ ይገኛል። የአፍሪካ ልማት ባንክም የካርቦን ገበያ የፋይናንስ አማራጭ በማዘጋጀት ሀገራት ማዕቀፎች እንዲቀርጹና የካርቦን ክሬዲት በአፍሪካ የአክሲዮን ገበያዎች ውስጥ እንዲካተቱ አድርጓል። የአፍሪካ ሕብረት የልማት ኤጀንሲ (አውዳ-ኔፓድ) በአህጉሪቷ የካርቦን ገበያ ቀረጻ፣ ትግበራ እና የግብይት ስርዓቱን የሚወስን “African Gold Standard” የተሰኘ የአሰራር ማዕቀፍ አዘጋጅቶ እየተገበረ ይገኛል። ማዕቀፉ የካርቦን ገበያ ማህበረሰቦች ካርቦንን በማመቅ ስራቸው ተጨባጭ ተጠቃሚነታቸው እንዲረጋገጥና ለብዝበዛ እንዳይጋለጡ ክትትልና ድጋፍ የሚደረግበት መንገድ ነው። የአየር ንብረት ጉባኤውን የምታዘጋጀው ኢትዮጵያ በካርበን ገበያ ተጠቃሚነቷን ለማረጋገጥ እየሰራች ትገኛለች። ኢትዮጵያ ሙቀት አማቂ ጋዞች ልቀት ቅነሳና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የ10 ዓመት መሪ የልማት እቅድ ቀርጻ ስትራቴጂካዊ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ እንደሆነች የፕላንና ልማት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። የእርምጃዎቹ አንድ አካል የሆነው የካርቦን ግብይትን በውጤታማነት ለመምራትና ተጠቃሚ ለመሆን ብሔራዊ የካርበን ግብይት ስትራቴጂ አዘጋጅታለች። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር በኢትዮጵያ የካርቦን ግብይት ስትራቴጂ የመጨረሻ ረቂቅ ግምገማ እና የካርቦን ገበያ የህግ ማዕቀፍ የህግ ክፍተት ዳሰሳ ጥናት ሪፖርት (Validation Worksop on draft Ethiopia’s National Carbon Market Strategy and Consultation on the Legal Gap Analysis Report) ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በግንቦት ወር 2017 ዓ.ም በቢሾፍቱ አካሄዶ ነበር። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ስትራቴጂውን በፍጥነት ወደ ስራ ለማስገባት ከስትራቴጂ ዝግጅቱ ጎን ለጎን የካርቦን ገበያ ሊመራበት የሚችል የህግ ማእቀፍ ለማዘጋጀት የህግ ክፍተት የዳሰሳ ጥናት መካሄዱን ገልጸዋል። የማዕቀፉ ዓላማ በኢትዮጵያ በአግባቡ ተግባራዊ ሊደረግ የሚችል የህግ ማዕቀፉን በፍጥነት አዘጋጅቶ በማጸደቅ የካርቦን ግብይት ላይ በንቃት እና የኢትዮጵያን ተጠቃሚነት ባረጋገጠ መልኩ መሳተፍ እንደሆነ ተናግረዋል። በመድረኩ ላይ የካርቦን ገበያ ልማት ስትራቴጂ ረቂቅ ሰነድ እና የካርቦን ገበያ ንግድ የህግ ማዕቀፍ ዳሰሳ ጥናት ሰነድ ግብአቶችን አካቶ በማዳበር ያሉትን ሂደቶች በማለፍ በቅርብ ጊዜ ወደ ስራ እንዲገባ አቅጣጫ ተሰጥቷል። ብሔራዊ የካርቦን ገበያ ሽያጭ ስትራቴጂ መዘጋጀቱ ኢትዮጵያ በደን ልማት፣በትራንስፖርት፣ በቆሻሻ አወጋገድና በኃይል አማራጭ ልማት ላይ በምታበረክተው ልክ ተጠቃሚ የሚያደርጋት መሆኑን ሚኒስቴሩ ገልጿል። በዚህም ሙቀት አማቂ ጋዞችን በመቀነስ፣ አረንጓዴ ኢኮኖሚ በማሳለጥና የዜጎችን ተጠቃሚነት በማሳደግ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስራን ለማገዝ ጉልህ ፋይዳ ያለው መሆኑን አመልክቷል። ኢትዮጵያ ከኖርዌይ በየካቲት ወር 2016 ዓ.ም የተፈራረመችው የ75 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የካርቦን ሽያጭ ስምምነት በካርቦን ግብይቱ እያገኘች ያለውን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት የሚያሳይ ነው። እ.አ.አ እስከ 2026 ድረስ የሚቆየው ስምምነት ከካርበን ሽያጭ የሚገኘውን ገቢ እንደ ሀገር የተሰሩ የአረንጓዴ ልማት ስራዎችን ለማጠናከር እንዲሁም አዳዲስ የደን ልማት ስራዎችን ለመስራት ይውላል። በባሌና ምዕራብ አርሲ ጥብቅ ደኖች ሲተገበር በቆየው የበካይ ጋዞች ቅነሳና የደን ጭፍጨፋን የመቀነስ ፕሮጀክት (ሬድ ፕላስ) አማካኝነት እየተከናወነ ያለው የካርቦን ንግድ በሚሊዮኖች ብር የሚቆጠር ብር ገቢ እየተገኘበት ነው። ፕሮጀክቱ በመተግበሩ ጉዳት ይደርስበት የነበረው የደን ሀብት መጠበቅ እና የካርቦን ጋዝ ልቀትን ማስቀረት ተችሏል። ኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ የካርቦን ገበያ ተጠቃሚነቷን ለማሳደግ በሀገሪቷ የተለያዩ ጥብቅ ደኖች ካርቦኖችን በማከማቸት ገቢ እንዲገኝ እየሰራች ነው። የካርቦን ግብይት የኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ የማግኘት አማራጭ በማስፋት ረገድ ቁልፍ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ በመገንባት እና የካርቦን ገበያ የአሰራር ማዕቀፍ በመዘርጋት እያከናወነች ያለው ስራ ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው። በሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤም በካርቦን ገበያ ያላትን ተሞክሮ ታቃርባለች ተብሎ ይጠበቃል። በጉባኤው ላይ የካርቦን ገበያ የበካይ ሀገራት እና ኩባንያዎች የገንዘብ መክፈያ ዘዴነት ወጥቶ በአፍሪካውያን ባለቤትነት እንዲመራ መሪዎች ጠንካራ ጥሪ እንደሚያቀርቡ ይጠበቃል። አፍሪካ በጉባኤው ላይ ጠንካራ የካርቦን ገበያ አስተዳደር ስርዓት መገንባት፣የካርቦን ክሬዲት ሽያጭ ላይ የሚያጋጥሙ የክፍያ ክፍተቶች ዘላቂ መፍትሄ እንዲያገኙ ማድረግ፣ የማህበረሰብ ተጠቃሚነትን የበለጠ ማረጋገጥ፣ ተጠያቂነትን ማስፈን እና ፍትሃዊ ገቢ ማግኘት ላይ ለውጥ የሚያመጡ ውሳኔዎችን ማሳለፍ እንዳለባቸው የዘርፉ ባለሙያዎች ይመክራሉ። የካርቦን ገበያ በተገቢው ሁኔታ የሚፈጸም እና የአፍሪካን ባለቤትነት የሚያረጋግጥ ከሆነ ለአህጉሪቷ ዘላቂ የፋይናንስ አማራጭ፣ አይበገሬነትን ለመገንባት እና ዘላቂ እድገትን ለማምጣት ወሳኝ ሚና ይጫወታል።
አሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል- የልጃገረዶች የባህል ፈርጥ
Aug 24, 2025 417
አሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል- የልጃገረዶች የባህል ፈርጥ በእንግዳው ከፍያለው የነሃሴ ወር የልምላሜ ምልክት ነው። ከሰኔ አጋማሽ ጀምሮ የሚዘንበው ዝናብ ፍሬው የሚታየው በነሃሴ ወር ምድርን በሚያለብሰው ቡቃያና የሳር ልምላሜ ነው። በዚህ ወር ሌት ከቀን የሚጥለው ዝናብ፣ በነፋስ የሚታገዘው ውሽንፍር፣ ውርጩና ቁሩ ሳይበግራቸው ልጃገረዶች ይሰባሰባሉ። የአሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል በዓልን ለማከበር በእድሜ እኩያቸውና እንደየሰፈር ቅርበታቸው ቡድን ይመሰርታሉ። ቡድን መመስረት ብቻ ሳይሆን “አሸንድዬ አኽ፤ አሸንዳ ሆይ፤ እሽ እርግፍ አትይሞይ፤…” የሚለውን የበዓሉን ማድመቂያ ጭፈራ መለማመድ ይጀምራሉ። ከልምምዱ ጎን ለጎንም ለጆሯቸው ጉትቻ፣ ለአንገታቸው ድሪ፣ ማርዳ፣ ጠልሰምና ማሰሪያ የተለያየ ቀለም ያላቸው ክሮችን በመሰብሰብ ያዘጋጃሉ። ለእጃቸው አምባር፣ ለእግራቸው አልቦና ሌሎች ጌጣጌጦችን ያፈላልጋሉ፤ ያሰባስባሉ፣ ያመቻቻሉ። ጌጣጌጦቹ ከእናቶቻቸው፣ ታላቅ እህቶቻቸውና ሌሎች ቤተሰቦችም ጭምር የሚሰበሰቡ ናቸው። አዲስ የሚገዛ ገዝቶ ወይም ለክት የተቀመጠውን በማውጣት አልባሳት ያዘጋጃሉ። በበዓሉ ዋዜማ ለባህላዊ ጭፈራው ስያሜ መነሻ የሆነው “አሸንዳ” እየተባለ የሚጠራውን ረጃጅም ቅጠል ያለውን ተክል በማምጣት በወገብ ለማሰር በሚያመች መልኩ ተጎንጉኖ በጓሮ ጤዛ በያዘ ሳር ተሸፍኖ እንዲያድር ይደረጋል። ይህ የሚደረገው ጠንዝሎ እንዳይበጣጠስ ነው። የጸጉር ስሬትም ምን ዓይነት መሆን እንዳለበት፤ ጥሩ ጸጉር ሰሪ ማን እንደሆነች በመነጋገር ቀድመው ወረፋ ያስይዛሉ። ለጸጉር ሰሪዋም በአይነትም ሆነ በብር ክፍያ ይዘጋጃል፤ ቀደም ሲል በነጻ እንደነበርም ይነገራል። ይህ ሁሉ ዝግጅት የልጃገረዶች በዓል የሆነውን የአሸንድዬ፣ ሻደይ፣ ሶለል በዓል በጋራ ለማክበር ነው። ዝግጅቱን ለሚያይ ሰው “ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ፤ ይበጣጠስ” የሚለውን የሀገሬውን ብሂል ለአሸንድዬ ያልሆነ ቀሚስ ... የተባለ ነው የሚያስመስለው። ማህበረሰቡ በየቤቱ ምግብና መጠጥ በማዘጋጀት እርስ በእርስ በመጠያየቅ የሚያጅብበት በዓልም ነው። ድፎ ዳቦ፣ ሙልሙል ዳቦ፣ ጠላ፣ ጠጅና ሌሎች የምግብና የመጠጥ አይነቶች በየቤቱ ማዘጋጀት የተለመደ ነው። ልጃገረዶች በየቤቱ እየዞሩ ሲጨፍሩ አንዱ ስጦታ ሙሉሙል ዳቦ ይሆናል ማለት ነው። በዓሉ የሚከበርባቸው አካባቢዎችም በሰሜን ወሎ ዞን ላሊበላ፣ ቡግና፣ መቄት፣ ግዳን፣ ቆቦ፣ ጉባላፍቶና መርሳ አካባቢዎች ሲሆን በዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር በሁሉም ወረዳዎች በድምቀት ይከበራል። በዓሉ ከጥንት ጀምሮ በአካባቢው ማህበረሰብ ዘንድ በድምቀት የሚከበር ነው። ከነሃሴ 16-21 በሚከበረው የበዓል ሳምንት ሴት ልጆች ከብት እንዲጠብቁ አይገደዱም፣ ሌላ ስራም እንዲሰሩ አይጠየቁም። ምክንያቱም እለቱ ለእነርሱ የነፃነት ቀናቸው ነውና። በዓሉ በልጃገረዶች ጭፈራ ብቻ የሚከበር ሳይሆን በታዳጊና ወጣት ወንዶች ጅራፍ ግርፊያና ማጮህ ታጅቦ የሚከበር ነው። የአሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል በዓል በአካባቢው ባህል ተጨማሪ እሴት ያለው በዓል ነው። ለመተጫጨት ምቹ አጋጣሚ የሚፈጥር በዓልም ነው። በዓሉ ከመተጫጨትም ባለፈ ለሌሎች ማህበራዊ ትስስሮች ፋይዳው የጎላ ነው። ልጃገረዶች በመሰረቱት ቡድን አምረው ለብሰውና ከጸጉር እስከ እግራቸው በተለያዩ ጌጣጌጦች ተውበው በዓሉን እያዜሙ ያከብራሉ። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በዓሉ ከሰፈር ወጥቶ ትልቅ ትኩረትም አግኝቶ በየአደባባዮች መከበር ይዟል። በዚህም የውጭና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎችን ቀልብ እየሳበ በአካበቢው ከሚገኙት ታሪካዊ የመስህብ ሃብቶች በተጨማሪ አዲስ የመስህብ ምንጭ እየሆነ መጥቷል። ይህንን ድንቅና ታሪካዊ እሴት በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባሕል ድርጅት /ዩኒስኮ/ በማስመዝገብ ኢትዮጵያን እንዲያስተዋውቅና ዓለም አቀፍ የቱሪዝም መስህብ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። የዘንድሮው የአሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል በዓል ታሪካዊና ባህላዊ እሴቱን ጠብቆ በደማቅ ስነ ስርአት ተከብሯል። የበዓሉ አከባበር ባህላዊ እሴቱን አጉልቶ በማሳየት፣ ለሀገር ገጽታ ግንባታ፣ ለቱሪዝም ሃብት ምንጭነትና ለኢኮኖሚ ማንሰራራት የላቀ ፋይዳ እንዳለውም ይታመናል።
በይቅርታ የታደሰ ህይወት
Aug 22, 2025 507
በይቅርታ የታደሰ ህይወት... ወጣት ዘውዱ ማሞ ትውልድና እድገቱ በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ጋዝጊብላ ወረዳ ዛሮታ ቀበሌ ነው። በስራው ስኬታማ ለመሆንና ኑሮውን ለማሸነፍ ሁሌም የሚተጋው ዘውዱ ከእለታት አንድ ቀን የተወሰኑ ግለሰቦች ያለበት ድረስ በመሄድ ያልሆነውን ሆኗል ወደፊት ደግሞ እንዲህ ይሆናል እያሉ አሉባልታ በማውራት የተሳሳተ መንገድ እንዲከተል ሊያሳምኑት ሞከሩ። ለመልእክተኞቹም ሰርቶ ለመለወጥ፣ ቤተሰቦቹን ለማገዝና በአካባቢው የልማት አጋር፣ የሰላም ቀናኢ መሆን እንጂ እነርሱ የሚሉትን መንገድ እንደማይመርጥ ደጋግሞ ነገራቸው። የሚደጋገም ነገር በሰዎች አዕምሮ ላይ ጫና እና ጥርጣሬ መፍጠሩ አይቀርምና በምልልስ ሃሳባችንን ተቀበል የሚሉት ሰዎች ምን እያሉኝ ነው፣ ምንስ ፈልገው ነው የሚለውን ጉዳይ ማሰላሰሉ አልቀረም። የጋዝጊብላው ወጣት ቆይቶም በመልእክተኞቹ የጥፋት አጀንዳ መሸነፉ አልቀረም፤ እሽታውን ገልፆላቸው ህዳር 2016 ዓ.ም ጠመንጃ አንግቶ ተከትሏቸው ጫካ ገባ። የጫካ ህይወትንም አንድ ብሎ በመጀመር በአካባቢው የጥፋት አጀንዳ ይዘው ከተነሱት ጋር እርሱም ተቀላቅሎ ጥፋትን የዘወትር ስራው አደረገው። ከዚህ የጥፋት ቡድን ጋር በጫካ እየተሹለከለከ የአካባቢውን ነዋሪ እየዘረፈ፣ እየበደለና እየገደለ መዝለቅ ለምን? የሚለው ጥያቄ ግን በአዕምሮው ያቃጭልበት ይዟል። በዚህ ሂደት ከጥፋት ቡድኑ የሚላቀቅበትንና የሚወጣበትን መንገድ እያሰበ ከቆየ በኋላ ተሳክቶለት መንግስት ያቀረበውን የሰላም ጥሪ ተቀብሎ ትጥቁን በመፍታት ቤተሰቦቹን ዳግም ተቀላቅሏል። በራስ ህዝብና በቤተሰብ ላይ በመሸፈት መግደል፣ መዝረፍና ማገት ለምን? የሚለው ዘውዱ፤ እኔ ባጠፋሁት ሁሉ ይቅርታ ጠይቄ ተመልሻለሁ፤ ሁላችሁም ተመለሱ በማለት መልእክቱን አስተላልፏል። በጥፋቱ በመፀፀት ሕብረተሰቡን ለመካስ ቃል በመግባት የልማት አርበኛ የሰላም አምባሳደር በመሆን ለማገልገል ዝግጁ መሆኑን አረጋግጦ፤ በይቅርታ የታደሰው የዘውዱ ህይወቱ ቀጥሏል። አሁን የተለያዩ የግብርና ስራዎች ላይ ተጠምዶ ኑሮን ለማሸነፍ ደፋ ቀና እያለ ያለው ዘውዱ በተጓዳኝ የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች ጥገና እና ሌሎችንም ስራዎች በማከናወን ላይ ይገኛል። የትጥቅ እንቅስቃሴ ለማንም ቢሆን ኪሳራ እንጂ ትርፍ እንደሌለው በተግባር አይቻለሁ የሚለው ዘውዱ የሰላም አማራጭ ሁሉንም አሸናፊ የሚያደርግ መሆኑን አንስቷል። በመሆኑም ሰላም በመንግስት ጥረት ብቻ የሚመጣ ባለመሆኑ ሁሉም የሰላም አምባሳደርና የልማት አርበኛ መሆን ይኖርበታል ሲል አንስቷል። የጋዝጊብላ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አበባው ደሳለኝ፤ የዘውዱ መልካም ተግባር በጥፋት መንገድ ላይ ያሉ ሁሉ ከተግባራቸው እንዲመለሱ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል። ከነበረበት የተሳሳተ መንገድ ወጥቶ አሁን ላይ በልማት ከፊት የሚሰለፍ፣ ለሰላምና መረጋጋት የሚተጋ የሰላም አምባሳደር ሆኗል ብለዋል። አጠቃላይ ሕብረተሰቡንና የሃይማኖት አባቶችን ያሳተፈ የሰላምና የፀጥታ ስራ በመከናወኑ በጥፋት መንገድ ላይ የነበሩ ታጣቂዎች እየተመለሱ መሆኑን ገልጸው ሌሎችም የተሰጠውን እድል እንዲጠቀሙ ጥሪ አቅርበዋል። የብሔረሰብ አስተዳደሩ የሰላምና ፀጥታ መምሪያ ኃላፊ ሃምሳ አለቃ አዘዘው አዳነ፤ ከሃገር ሽማግሌዎችና ከሃይማኖት አባቶች ጋር በመቀናጀት በተከናወነው ስራ በቅርቡ ብቻ 336 የቀድሞ ታጣቂዎች የሰላም ጥሪ ተቀብለው መግባታቸውን ተናግረዋል። በተሳሳተ መንገድ ጫካ ገብተው ያልተመለሱ ቀሪ ታጣቂዎችም የቀረበላቸውን የሰላም ጥሪ ተቀብለው በአፋጣኝ እንዲመለሱ አሁንም በሩ ክፍት መሆኑን አረጋግጠዋል።
ማኅበራዊ መሥተጋብርን የሚያጸናው - ቡሔ
Aug 18, 2025 464
(በዮሐንስ ደርበው) ሰዎችን ከንጥል እሳቤ እያፋቱ የወል አመለካከት በመትከል ማኅበራዊ መሥተጋብርን የሚያጸኑ ዕሴቶች ከሚገኙባቸው ሁነቶች መካከል በዓላት ይጠቀሳሉ። ከእነዚህ በዓላት መካከል ደግሞ ሰሞኑን እየተከበረ ያለው ቡሔ (ደብረ ታቦር) አንዱ ነው፡፡ ቡሔ የቃሉ ፍቺ “መላጣ፣ ገላጣ” ማለት ነው ይላሉ በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት ቀሲስ አንድነት አሸናፊ። በሀገራችን ክረምቱ አልፎ የብርሃን ወገግታ የሚታየው በዚሁ በዓል ወቅት አካባቢ ስለሆነ “ቡሔ” የተባለው በዚህ ምክንያት ነው ይላሉ። ይህም ከኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሁኔታ ጋር የተቆራኘ መሆኑን ይናገራሉ። ቡሔ ደብረ ታቦር እየተባለ እንደሚጠራም ያነሱት መምህሩ፤ "ቡሔ ከሚለው ይልቅ ደብረ ታቦር የሚለው መጠሪያ የተሻለ" ስለመሆኑ ይገልጻሉ፡፡ የደብረ ታቦር በዓል ታሪካዊ አመጣጡ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 17 ከቁጥር 1 እስከ 9 ያለው ቃል መሆኑንም አንስተዋል። በዚሁ ምዕራፍ ቁጥር 1 ላይ ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን ይዞ ወደ ተራራ በመውጣት በታቦር ተራራ ላይ ብርሃነ መለኮቱን ስለመግለጡ መገለጹን ጠቅሰው፤ በየዓመቱ ነሐሴ 13 የሚከበረው የቡሔ (ደብረ ታቦር) በዓል መነሻም ይህ መሆኑን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋኅዶ ቤተ-ክርስቲያንም ከዘጠኙ ዐበይት በዓላት መካከል አንዱ አድርጋ ትቀበለዋለች ይላሉ መምህር ቀሲስ አንድነት። በዓላት በሐይማኖት ውስጥ ሁለት ዓላማ እንዳላቸው አስገንዝበው፤ አንደኛው ሰውና እግዚአብሔርን ማገናኘነት ሲሆን ሁለተኛው ሰውና ሰውን ማገናኘት መሆኑን አብራርተዋል፡፡ ስለዚህ በቡሔ በዓል ምክንያት ሰዎች ይገናኛሉ፤ ሰዎች ሲገናኙ ደግሞ በፍቅር፣ በእርቅ፣ ማዕድ በመጋራት ነው ይላሉ። በተለይም በቡሔ በዓል ላይ የዝክር፣ ዳቦ የመስጠት፣ የጎረቤት መጠያየቅ፣ የተቸገረን የመርዳት፣ እነዚህን የመሳሰሉ ማኅበራዊ መሥተጋብርን አጽኚ፣ አቀራራቢ እና አሰባሳቢ ዕሴቶች እንደሚተገበሩ ያስረዳሉ፡፡ ቡሔ በርካታ ትውፊቶች እንዳሉት የሚናገሩት መምህር ቀሲስ አንድነት፤ ከእነዚህ መካከል ችቦ፣ ሙልሙል (ዳቦ)፣ ጅራፍ እና ዝክር የሚሉትን ጠቅሰዋል፡፡ የሚበራው ችቦ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን የመግለጡ ምሳሌ ነው ብለዋል፡፡ ችቦው ብርሃንነትን ስለሚያሳይ ደቀመዛሙርቱ ብርሃኑን ዐይተው መውደቃቸውን ለማሳየት ነው ይላሉ፡፡ እንዲሁም ሙልሙል (ዳቦ) ደግሞ ደቀመዛሙርቱ በደብረ ታቦር በነበሩ ጊዜ ያን ለማየት የሄዱ ቤተሰቦቻቸው ይዘውላቸው ከመጡት ምግብ ጋር የሚገናኝ መሆኑን ነው የሚያስረዱት። በቡሔ የጮኸው ጅራፍም “አብ በደመና ሆኖ የምወደው ልጄ እርሱ ነው፤ ይህን ስሙት ያለው” ምሳሌ ነው፤ የብርሃኑ መንጸባረቅ በደብረ ታቦር የነበረው ብርሃነ መለኮቱ ሲንጸባረቅ ብርሃን ታዬ ስለሚል የእዛ ምሳሌ ነው ሲሉም ያስረዳሉ፡፡ ከቡሔ ትውፊቶች አንዱ ዝክር መሆኑን ገልጸው፤ በተለይ የቡሔ በዓል በገጠር በአብነት ትምህርት ቤት የተማሪዎች ዝክር የሚደረግበት መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም ጎረቤት ለጎረቤቱ፣ ደቀመዛሙርት ለመምህሮቻቸው፣ ምዕመናን ለሌሎች ሰዎች ያካፍላሉ ነው ያሉት፡፡ በተጨማሪም በየቤቱ ሂደው ቡሔን የሚያከብሩ፣ በዓሉ ሲከበር ምጽዋት እና ዳቦ የሚቀበሉ ልጆች ደግሞ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱ ሲገለጥ የሄዱ ወላጆች ልጆች ምሳሌ መሆኑን በመግለጽ፤ እነዚህ በሂደት የተላለፉልን ትውፊቶች ናቸው ብለዋል፡፡ በአጠቃላይ ቡሔ በልጆች፣ በወጣቶች፣ በሕብረተሰቡ ዘንድ መቀራረብን በማጠናከር ረገድ በጎ አስተዋጽዖ እያሳደረ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ለምሳሌ አንዳንዶች ልጆች ቡሔን በየዓመቱ ያስቀጥላሉ፤ ሌሎች ሲያደርጉ ዐይተው የሚቀላቀሉም አሉ፤ በዚህ ሂደት ነባሮቹ አዲሶቹን በመቀበል ግጥሙን ያስጠናሉ፤ ባህሉንና ትውፊቱንም እንዲጠብቁ ያስተምራሉ፤ በእነዚህ ሂደቶች አይዞህ በርታ እየተባባሉ መደጋገፍና መመሰጋገን አለ ነው የሚሉት። አሁን አሁን በተለይ በከተማ አካባቢዎች ላይ ቡሔ በአግባቡ ሲከናወን አይስተዋልም ይላሉ። ልጆቻችን ማኅበራዊ ሚዲያ እና ኮምፒውተር ላይ ብቻ ተጣብቀው ባህላዊውን ነገር እየረሱት በመሆኑ ቡሔን በትክክል እንዲያውቁት ማድረግ ከወላጆች እና ማኅበረሰቡ ይጠበቃል ነው ያሉት። እንደ መምህር ቀሲስ አንድነት ገለጻ፤ ልጆች ሆያሆዬ የሚሉት ለበዓሉ ክብርና ለስሜታቸው ነው። ምንም እንኳን ልጆች የገንዘብ ችግር ኖሮባቸው ባይሆንም ሆያሆዬ የሚሉት ከሆያሆዬ ጭፈራው በኋላ ገንዘብም ዳቦም እንደሚሰጥ ይናገራሉ። ዳቦው ለትውፊቱ፤ ገንዘቡ ደግሞ ለልጆቹ ድካም እና የትምህርት ቁሳቁስ ማሟያ ስለሚሆን አንድም ማኅበራዊ ኃላፊነትን ለመወጣት እና ለመተጋገዝ መልካም አጋጣሚ ይሆናል ይላሉ። ቃሉ “እርሱን ስሙት” ብሏልና በየደረጃው ከቤተብ እስከ ሀገር በመደማመጥ ከቡሔ (ደብረ ታቦር) መሰባሰብን፣ መግባባትንና መተሳሰብን መውሰድ እንደሚገባ ይመክራሉ። መንግሥት ወይም ሕዝብ በሚሠራው ነገር ብቻ ሀገርን መገንባት እንደማይቻል ጠቅሰው፤ በደብረ ታቦር ክርስቶስ እንደሰጠው ትክክለኛ ምስክርነት ባልና ሚስት፣ ወላጆችና ልጆች፣ አሠሪና ሠራተኛ፣ መንግሥትና ሕዝብ፣ ትልቅና ትንሽ፣ ካህን እና ምዕመን ሁሉም እየተደማመጡና እየተግባቡ ለአንድ ዓላማ በጎ ዐሻራ ማኖር አለባቸው ይላሉ። ለዚህ ደግሞ ሁሉም የራሱን ኃላፊነት ሲወጣ ነው ሀገርዊ ፋይዳ ሊኖረው የሚችለው ብዬ አምናለሁ ብለዋል፡፡
አፍሪካውያን ለዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ፍትህ የሚጠይቁበት ጉባኤ
Aug 16, 2025 470
አፍሪካ የምንኖርባትን አለም ህልውና የሚያስጠብቅ እና የሚያስቀጥል ጠንካራ ኃይል ያላት አህጉር ናት ማለት ይቻላል። ከአማዞን ቀጥሎ ሁለተኛው የምድራችን ሳንባ እየተባለ የሚጠራው የኮንጎ ተፋሰስ በዚሁ አህጉር የሚገኝ ነው። ተፋሰሱ በርካታ ካርቦን ዳይኦክሳይድ አምቆ በመያዝ የአየር ንብረት ሚዛንን ይጠብቃል። እንደ አባይ፣ ኮንጎ እና ኒጀር የመሳሰሉ ወንዞች ከአፍሪካ ድንበር ተሻግረው በግብርና እና የስነ ምህዳር ጥበቃ ላይ እየተወጡት ያለው ሚና ትልቅ ነው። ከተንጣለለው የሳቫና የሳር መሬት እስከ ከርሰ ምድር የተፈጥሮ ጸጋዎች የአፍሪካ ብዝሃ ህይወት የዓለም ስነ ምህዳር በዘላቂነት እንዲቀጥሉ እያደረጉ ይገኛል። አፍሪካ ያላትን እምቅ የታዳሽ ኃይል ምንጭ በዓለም ንጹህ የኢነርጂ ኃይልን ለማስፋት ያለው ሚና ጉልህ መሆኑ አያጠራጥርም። አህጉሪቷ ዓለምን በተፈጥሯዊ ሀብቷ እየጠበቀች ቢሆንም እምብዛም ድርሻ በሌላት የአየር ንብረት ለውጥ ገፈት ቀማሽ ሆናለች። ተከታታይ ድርቅ እና ጎርፍ እንዲሁም የምግብ ዋስትና ማጣት ከቀውሶቹ መካከል ይጠቀሳሉ። የኢንዱስትሪ ዘመን አሃዱ ብሎ ከጀመረበት እ.አ.አ 1850ዎቹ አንስቶ ዓለም ላይ ከሚለቀቀው ካርቦን ዳይኦክሳይድ አፍሪካ ያላት ድርሻ ከ3 እስከ 4 በመቶ ብቻ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። በአንጻሩ የበለጸጉ ሀገራት በዓለም ለይ በካይ ጋዝን በመልቀቅ 80 በመቶ የሚሆን ድርሻ አላቸው። እነዚህ የበለጸጉ ሀገሮች እ.አ.አ በ2009 በዴንማርክ ኮፐንሃገን 15ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ -15) ላይ በአየር ንብረት ለውጥ ተጎጂ ለሆኑ በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በየዓመቱ 100 ቢሊዮን ዶላር ለመስጠት ቃል ቢገቡም ቃል ኪዳናቸውን እየጠበቁ አይደለም። ለአፍሪካ አህጉር ጨምሮ ለሌሎች በማደግ ላይ ለሚገኙ ሀገራት ያደጉ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመከላከል ቃል የገቡትን 100 ቢሊዮን ዶላር እንዲያሟሉ ጥሪ እያቀረቡ ይገኛል። አየር ንብረት ለውጥ ፈተና ውስጥ ባለበት በአሁኑ ወቅት አፍሪካዊያንን ለዚህ አንገብጋቢ አጀንዳ በጋራ የሚያቆም ሁነት ከፊት ለፊታችን እየመጣ ነው። ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ህብረት በጋራ የሚያዘጋጁት ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም በአህጉሪቷ መዲና አዲስ አበባ ይካሄዳል። ጉባኤው የአፍሪካ መሪዎች፣ አርሶ አደሮች፣ ተመራማሪዎች፣ ወጣቶች፣ ኢኖቬተሮች እና ለውጥ ፈጣሪዎች በአንድ ጥላ ስር የዘመኑ ትልቅ ፈተና በሆነው የአየር ንብረት ቀውስ እና መፍትሄው ላይ ይመክራሉ። ችግሩ አለ ብሎ ከማውራት ባለፈ እንደ አረንጓዴ አሻራ ያለ ሀገር በቀል የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄዎችም ይቀርባሉ። ጉባኤው የአፍሪካ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ላይ ፍትህ ሊሰጠን ይገባል የሚል ጠንካራ እና የጋራ ድምጽ የሚያሰሙበት ነው። አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የሚያስፈልጋትን ፋይናንስ የበለጸጉ ሀገራት እንዲሰጡም ጠንካራ ጥሪ ይቀርብበታል ተብሎ ይጠበቃል። 30ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ 30) በመጪው ህዳር ወር 2018 ዓ.ም በብራዚል ቤለም ከተማ ይካሄዳል። አፍሪካውያን በኮፕ 30 ላይ አህጉሪቷ ሊኖራት የሚገቡ አጀንዳዎችን እና የጋራ አቋሞችን ያዘጋጃሉ።በጉባኤው ከአዲስ አበባ የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄ ድምጽ ጎልቶ ይሰማል። ዓለም የሚቀርበውን ጥሪ ጆሮ ሰጥቶ በማዳመጥ በአየር ንብረት ለውጥ የተግባር ምላሽ እንደሚሰጥም ይጠበቃል።
ቆሻሻን ወደ ሀብት በመቀየር የተለወጠ ቤተሰብ
Aug 14, 2025 454
አቶ ሔኖግ ዶንጋቶ የሀዋሳ ከተማ ነዋሪ ናቸው። በሚኖሩበት ሀዋሳ ከተማ በ2005ዓም ኑሮን ለማሸነፍ ሲሉ ቆሻሻን በእጅ ጋሪ መሰብሰብ ጀመሩ፡፡ ስራቸውን ከጀመሩ ከአንድ ዓመት በኋላም በአንድ የአህያ ጋሪ ቆሻሻ የመሰብሰብ ስራቸውን ይበልጥ አጠናክረው ጠሉ። በሂደትም ከባለቤታቸው ጋር ሆነው በተለያዩ ድርጅቶች፣ መኖሪያ ቤቶች፣ ፋብሪካዎች፣ የህክምና ተቋማት በመሄድ ቆሻሻን በመሰብሰብና በመለየት መልሶ ጥቅም እንዲሰጥ በማድረግ ስራውን አስፋፉ ። በኋላም ስራቸውን የበለጠ አስፍተው ለመስራት በማሰብ በ2010 ዓ.ም ከ12 በላይ የቤተሰብ አባላትን በመያዝ “የሀዋሳ ውበት ደረቅ ቆሻሻ ማስወገድና መልሶ መጠቀም ህብረት ስራ ማህበር" በሚል ማህበር መሰረቱ። በሂደትም ቆሻሻን ወደ ሀብትነት በመቀየር ህይወታቸውን ከመለወጥ አልፈው ለብዙዎች የስራ ዕድል መፍጠር ቻሉ። አሁን ላይ ስራው ሰፍቶ በከተማዋ ታዋቂ ሆነዋል፤ የሀዋሳን ከተማ ቆሻሻ 35 በመቶ ይሰበስባሉ፡፡ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ እንዲሉ አካባቢን ማጽዳትን ከሚወገደው ቆሻሻ ደግሞ ገንዘብ ማግኘትን የዕለት ተግባራቸው አድርገዋል። ከየአካባቢው በወጣቶች የሚሰበሰበውን ቆሻሻ ገንዘብ ከፍለው በመረከብ አይረባም ተብሎ በተጣለ ቆሻሻ ሀብት ማካበት ተክነውበታል። ወደ ስራ ቦታቸው ጎራ ያለ ሰው ቆሻሻን ያመጡ ደንበኞቻቸው በሰልፍ ገንዘብ ሲቀበሉ ማየት የተለመደ ነው ፡፡ ''ቆሻሻ ለእኛ ሀብት ነው፤ የሚጣል ወይም የማይጠቅም የምንለው ቆሻሻ የለም' የሚሉት አቶ ሄኖክ አሁን ላይ የመኖሪያ ቤት፣የቤት መኪና፣አምስት ቆሻሻ ማንሻ ተሽከርካሪን ጨምሮ ሌሎች ሀብቶችን ማፍራት ችለዋል፡፡ ማህበሩ በቀጥታ ከ100 ለሚበልጡ ሰራተኞች ቋሚ የስራ ዕድል የፈጠረ ሲሆን ቆሻሻን ከተለያዩ አከባቢዎች በማሰባሰብ ወደ ማህበሩ የሚያቀርቡ የበርካታ ዜጎች የገቢ ምንጭ መሆኑንም ይናገራሉ ፡፡ በቀጣይም ፕላስቲክን የሚተኩ ምርቶች በማምረት በሀገሪቱ በማይበሰብስ ቆሻሻ ሳቢያ የሚፈጠረውን ችግር በአግባቡ ለመከላከል የበኩላችንን ለማበርከት እንሰራለን ሲሉም ይገልጻሉ። በሀገራችን በድግስና ለቅሶ ጨምሮ የፕላስቲክ ምርቶች በከፍተኛ ሁኔታ ጥቅም ላይ የሚውሉ ሲሆን በዚያው ልክ በአግባቡ መሰብሰብና ማስወገድ እንዲሁም መልሶ ለጥቅም እንዲውል የማድረግ ባህል ስለለሌን ለከፋ ችግር እየተዳረግን ነው ያሉት አቶ ሄኖክ ማህበሩ ይህን ችግር ለማስቀረት እየሰራ መሆኑንም ተናግረዋል ። ለዚህ መፍትሄ እንዲሆን በአሁኑ ሰዓት ከሀዋሳ ውጪ 24 አጎራባች ከተሞች ፕላስቲክና የማይበሰብሱ ቆሻሻዎችን የሚሰበስቡ ወኪሎች በማስቀመጥ ከከተሞች ጋር በትብብር እንዲሰበሰብ በማድረግ እንደሚቀበሉም አመልክተዋል፡፡ የሚበሰብሰውን ቆሻሻ ወደተፈጥሮ ማዳበሪያነት በመቀየር ለሽያጭ እንደሚያቀርቡ ገልጸው በዘንድሮ ዓመት ብቻ ወደ 300 ሺህ ብር የሚጠጋ ገንዘብ ከቆሻሻ በተቀየረ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ወይም ኮምፖስት ሽያጭ ማግኘታቸውን አመልክዋል፡፡ በስራቸው ትልቁ ተግዳሮትና ችግር ሆኖ የቀጠለው በማህበረሰቡ ውስጥ ቆሻሻን ለይቶ ያለማስቀመጥ መሆኑን ጠቅሰው በዚህ ላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ ግንዛቤ እያደገ የመጣ ቢሆንም ብዙ ሊሰራ ይገባል ብለዋል ። እንደ ሀገር የተጀመረው የጽዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የተነሳ ለውጦች መታየት የጀመሩ ቢሆንም የታሰበውን ግብ እንዲመታ ማህበረሰቡ ቆሻሻን ለይቶ በማስቀመጥና በተገቢው መንገድ በማከማቸት በቆሻሻ ስራ ለተሰማሩ ሰዎች ስራን ማቅለል ብቻ ሳይሆን አካባቢን ከቆሻሻ የጸዳ የማድረግ ሀላፊነቱን ሊወጣ ይገባል ሲሉም ያስገነዝባሉ። ቆሻሻን የመሰብሰብ ስራ ስንጀር በማህበረሰቡ ውስጥ ባለው አመለካከት የተነሳ እስከ መገለልና መሰል ጉዳቶች ቢደርሱብንም ጸንተን በመግፋታችን ዛሬ ኑሯችንን ከመቀየር አልፈን በርካቶች ህይወታቸውን እንዲቀይሩ ዕድል ፈጥረናል የሚሉት ደግሞ የማህበሩ የሒሳብ ክፍል ሰራተኛና የአቶ ሄኖክ ዶንጋቶ ባለቤት ወይዘሮ መሰረት ድጋሎ ናቸው፡፡ “ማህበሩ ቆሻሻ በአግባቡ ከተያዘ ሀብት መሆኑን በተጨባጭ እያሳየ ነው” ያሉት ደግሞ የማህበሩ ጀኔራል ማናጀር አቶ አልታዬ ዬቦ ናቸው። ይህን ስራ ባለፉት ዓመታት በማከናወን ገቢ ከማግኘት ባለፈ ሀገራዊ የጽዳት ስራ ላይ አስተዋጽኦ እያበረከትን ነው ብለዋል፡፡ በሀዋሳ ከተማና ሌሎች ወኪሎች ባሉባቸው ከተሞች ከግለሰቦች መኖሪያ፣ ከሆቴሎች ከተለያዩ ድርጅቶችና ፋብሪካዎች ቆሻሻ በመሰብሰብና በመለየት የሚመጣውን ለተፈጥሮ ማዳበሪያነት ቀሪውን ደግሞ መልሶ ለመጠቀም እንልካለን፤ በሂደቱም ፕላስቲክ በተፈጥሮ ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ከመከላከል ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል እየተፈጠረ ነው ሲሉ ተናግረዋል። ቆሻሻን ሰብስቦ ወደ ሀብትነት ለመቀየር በሚደረግ ስራ ትልቁ ተግዳሮት ቆሻሻን ለይቶ የማስቀመጥ ባህል ያለማደጉ ነው ያሉት አቶ አልታዬ በዚህ ላይ ግንዛቤ የመፍጠርና የማስተማር ስራ በባለድርሻዎች ሊተኮር ይገባል ሲሉ አመልክተዋል ።ዘርፉ ከፍተኛ የሆነ የሀብት ምንጭ ቢሆንም ብዙ ዜጎች ያልተሰማሩበትና ትኩረት ያልተሰጠው መሆኑን አንስተው በተለይም ወጣቶች ስራ የለም ከሚል አስተሳሰብ በመላቀቅ በማህበር በመደራጀት በየአከባቢያቸው ያለውን ቆሻሻ በመሰብሰብ ወደ ስራ ቢገቡ ለመቀበልና ልምድ ለማካፈል ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። በማህበሩ በቆሻሻ መዛኝነት የስራ ዕድል ተጠቃሚ የሆኑት አቶ አዲሱ ኩኬ ከመንግስት ስራ በጡረታ ከተገለሉ ከዛሬ ሁለት ዓመት ጀምሮ በማህበሩ በመቀጠር ቤተሰባቸውን በኢኮኖሚ የሚደጉሙበት ዕድል እንዳገኙ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም የቆሻሻ ሰብሰባ ስራ ያልተለመደ ቢሆንም ማህበሩ በፈጠረው በጎ ተጽዕኖ በርካቶች ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን አመልክተዋል ። በሲዳማ ክልል ደን፣ አካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን የአከባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ዳይሬክተር አቶ ዮሴፍ ቲቦ በክልሉ ከፕላስቲክ ብክለት የጸዳ አከባቢን ለመፍጠር በተቀናጀ መንገድ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል ። በዚህም አበረታች ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል ያሉት ዳይሬክተሩ በተለይም የጽዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄን ስኬታማ ለማድረግ ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ እንዲውል የሚያስችል አሰራር ላይ ትኩረት መደረጉን ለአብነት ጠቅሰዋል። በክልሉ በዘርፉ የተሰማሩ ማህበራት ቆሻሻን ወደ ሀብት በመቀየር ህይወታቸውን በማሻሻል ላይ መሆናቸውን ጠቁመው ከእነዚህም አንዱ “የሀዋሳ ውበት ደረቅ ቆሻሻ ማስወገድና መልሶ መጠቀም ህብረት ስራ ማህበር"ን ለአብነት ጠቅሰዋል። ማህበሩ የሀዋሳ ከተማን ውብና ጽዱ በተለይም ከፕላስቲክ ቆሻሻ ጽዱ ለማድረግ የሚከናወኑ ተግባራትን በእጅጉ እያገዘ እንደሚገኝ ጠቁመው የከተማዋን ቆሻሻ በስፋት በመረከብና ሰብሳቢዎችን በየአከባቢው በማስቀመጥ የመሰብሰብ ስራ እያገዘ ይገኛል ብለዋል ። በተጨማሪም በሲዳማ ክልል የሚገኙና ሌሎች አጎራባች ክልሎች ከተሞች ቆሻሻን በመሰብሰብ ወደ ሀብትነት በመቀየር ለብዙዎች ምሳሌ መሆኑን አመልክተዋል:: ማህበሩ ብቻ ሳይሆን ሌሎችም በዘርፉ የተሰማሩ አካላት የበለጠ እንዲበረታቱ ባለስልጣኑ የህይወት ክህሎት ግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናዎችን ጨምሮ የገንዘብና የቦታ አቅርቦት በማመቻቸት የማገዝና የመደገፍ ስራ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል:: በተለይም የጽዱ ኢትዮጵያ ዕሳቤን የበለጠ ማስፋት ጠቃሚ በመሆኑ ማህበራትን የማጠናከር ስራ በልዩ ትኩረት እንደሚከናወን ተናግረዋል ።
ከጉርስ እስከ ውርስ የሚዘልቅ ሃብት
Aug 14, 2025 336
(በሳሙኤል አየነው - አርባምንጭ)-ከጉርስ እስከ ውርስ የሚዘልቅ ሃብት... በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ምዕራፍ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር "በአንድ ሰው 40 ችግኝ" በሚል መሪ ሃሳብ በ2011 ዓ.ም ነበር የተጀመረው። በዚሁ መርሃ ግብር ከ4 ነጥብ 7 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ኢትዮጵያዊያን አሻራቸውን የማኖር ጥረታቸውን ቀጠሉ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነት በተጀመረው የአረንጓዴ ኢንሸቲቭ የተራቆቱ አካባቢዎች ከማገገማቸው ባለፈ የምግብ ሉአላዊነትን የማረጋገጥን ድርብ አላማ ሰንቆ ለተከታታይ ሰባት አመታት ዘልቋል። ኢትዮጵያዊያን በዘንድሮው መርሃ ግብር "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መርህ በአንድ ጀምበር ብቻ 714 ነጥብ 7 ሚሊዮን ችግኞችን በመትከል ምንም ነገር ማሳካት እንደሚችሉ በተግባር ያሳዩበት ታሪካዊ አጋጣሚ ሆኗል። ባለፉት አመታት የተተከሉ ችግኞች ውጤትና የዘንድሮውን ተሳትፎ የኢዜአ ሪፖርተር በአርባ ምንጭ እና አካባቢው ነዋሪዎችን አነጋግሯል። የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪ አቶ ተዘራ ቀፃዮ፤የአረንጓዴ አሻራ የተቆረጡ ዛፎችን በመተካት የተራቆቱ አካባቢዎችን ማልበስ ያስቻለና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እድል ፈጥሯል ብለዋል። የዚህ ስኬት ሚስጢሩ በተባበረ ክንድ መስራትና ለቁም ነገር ማብቃት በመቻላችን ነው ሲሉም አስረድተዋል። ሁሉን ከዳር ዳር ያነቃቃው ይህ ሀገራዊ ፕሮጀክት ተከታታይነት ያለው ሰፊ አሻራ እንድናኖር ያደረገ ነው ያሉት አቶ ተዘራ አሻራችንን እያኖርን፣ ከተፈጥሮ ጋር እየታረቅን እያለማንና እየተጠቀምን ከጉርስ እስከ ውርስ የሚዘልቅ ሃብት እየፈጠርን እንገኛለን ብለዋል። በምድረ ገነትነት የምትታወቀው አርባምንጭ እና አካባቢው ባለፉት ዓመታት የአረንጓዴ ካባ እየለበሰ ይበልጥ ውብ እና ማራኪ እየሆነ መምጣቱንም አንስተዋል። ለአርባ ምንጭና አካባቢው ነዋሪዎች ችግኝ መትከልና መንከባከብ ልምድ እየሆነ መምጣቱን የተናገሩት አቶ ተዘራ ለመጪው ትውልድ ምቹ አካባቢን የመፍጠር ስራ በተጠናከረ መልኩ ቀጥሏል ብለዋል። በአርባምንጭ ከተማ የ"ነህሚያ" እንስሳት እርባታና ማድለብ ማህበር ሰብሳቢ ወጣት ህዝቅኤል ኦሎባ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተፈጥሮን ከመጠበቅም ባለፈ ከድህነት የመውጫ ሁነኛ መፍትሄ እየሆነ መጥቷል ብሏል። የአረንጓዴ አሻራ ልማት በአንድ በኩል ለደን ጥበቃና እንክብካቤ በሌላ በኩል ለእንስሳት መኖ እየዋለ ሲሆን በፍራፍሬ ልማትም የምግብ ዋስትና መሰረት እያኖረ መሆኑን አንስቷል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ከኢትዮጵያም ባለፈ ከጎረቤት አገራት ጋር የጋራ ልማትና ተጠቃሚነትን እያረጋገጠ ያለ ስለመሆኑም አስረድቷል። በመሆኑም አሻራችንን በማኖር ሀገርን ማልማት፤ ለነገ የሚሆን ጥሪት ማኖርና የትውልዶች ውርስ እንዲሆን የሁላችንም ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል ብሏል። በክልሉ ርእሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ሃሳብ አመንጭነት በ12 ዞኖች የአንድ ተራራ ልማት ኢኒሸቲቭ ተግባራዊ እየተደረገ ሲሆን በዚህም የከተማው ራስጌ ላይ የሚገኘው የጋንታ ተራራ ልማት ለአብነት የሚጠቀስ ሆኗል። በቅርቡ በዚሁ ተራራ ላይ አሻራቸውን ያኖሩት የብልጽግና ፓርቲ የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ሃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)፤ የአርባዎቹ ምንጮች ቤትና የእምቅ ተፈጥሮ ሃብቶች ባለቤት የሆነው አርባ ምንጭ ይበልጥ እያማረበትና እየተዋበ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ሃይል እና የአረንጓዴ አሻራ ልማት የሰውን ልጅ ከተፈጥሮ ጋር የሚያስታርቅ፣ ሀገርን የማልማትና የምግብ ዋስትና መሰረት መሆኑን ተናግረዋል። ከመጪው ትውልድ የተበደርነውን የተፈጥሮ ሀብት በመጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድ ምቹ ሀገር የማስረከብ ታሪካዊ ሃላፊነት አለብን ሲሉም አስገንዝበዋል። የአረንጓዴ አሻራ ልማት፣ የህዳሴ ግድብ ስኬት፣ በግብርና፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪ እና አይ ሲቲ ጭምር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የጋራ ትርክት መገለጫዎችና ለኢትዮጵያ ብልጽግና ተስፋ የተሰነቅንባቸው መሆኑን ተናግረዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደን፣አከባቢጥበቃና ልማት ቢሮ ሃላፊ ግዛቴ ግጄ፤ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ የመገንባት ራዕይ መሳካት በክልሉ ተጨባጭ ማሳያዎች መኖራቸውን አንስተዋል። የአረንጓዴ አሻራ ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት እንዲሁም ለሌማት ትሩፋት የላቀ ትርጉም እንዳለው አንስተው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በመሆኑም ችግኞችን መትከል ብቻ ሳይሆን ጥበቃና እንክብካቤ በማድረግ ተፈጥሮን ማልማትና የምግብ ዋስትና መሰረት ማኖር ይገባል ብለዋል። በክልሉ በ12 ዞኖች በመንግስት፣ በግለሰብ፣ በማህበራትና መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች 1 ሺህ 495 ችግኝ ጣቢያዎች መኖራቸውን ጠቅሰው በእነዚህም ለምግብነትና ሌሎችም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማፍላት ስራ በመከናወን ላይ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ በመትከል የማንሰራራት ዓላማ በመሰነቅ ለአረንጓዴ ልማት ስኬት እየተጋን እንገኛለን ብለዋል።
በደን ውስጥ ያረፈ አረንጓዴ አሻራ ምግብ እና ገንዘብ የሆነባት - ቤንች ሸኮ ዞን!
Aug 1, 2025 1047
(በቀደሰ ተክሌ) በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ውስጥ የሚገኘው የቤንች ሸኮ ዞን አረንጓዴና የምድር ገነት ከሚባሉ አካባቢዎች አንዱ ነው። ይህ አካባቢ በተፈጥሮ የተቸረው ሰፊ የደን ሽፋን ያለው ሲሆን ደኑ ክብሩን ጠብቆ ከዘመን ዘመን የመሸጋገሩ ምሥጢር ደግሞ በአካባቢው ብሔረሰቦች ዛፍ መቁረጥን እንደ ነውር የማየት ባህል መሆኑ ነው። በአካባቢው ዛፍ መቁረጥ ነውር ነው። ደፍሮ ያለአግባብ ቆርጦ ዛፍን ከቦታው የሚያጠፋ በአካባቢው ሽማግሌዎች ይረገማል። በዞኑ ዛፍን ቀርቶ ከዛፉ ጋር ተያይዞ የወጣን ሐረግ እንኳ በዘፈቀደ መቁረጥ አይፈቀድም። ለቤት መሥሪያና ሌሎች አገልግሎቶች ለመጠቀም ሲፈለግ እንኳን ጥቅጥቅ ያለ ደን እንዳይሳሳ አለፍ አለፍ ብሎ በጥንቃቄ የመቁረጥ ተሞክሮ አላቸው። ለቤንች ሸኮ ዞን ነዋሪዎች በቤታቸው ቅርበት ላይ ዛፍ መትከል ቅንጦት ሳይሆን እንደ መሠረታዊ የኑሮ ዘዬ ተደርጎ ይቆጠራል። በአረንጓዴ ልምላሜ ያልተከበበ ቤት የሰነፍ ቤት ነው። ከዛፎቹ አንዱ ቢቆርጥ እንኳ ሌላ ከስር ይተካል እንጂ እንዲሁ አይተውም። የአካባቢውን ልምላሜና አረንጓዴ ገጽታን ጠብቆ ያቆየው ይህ ባህል የቤንች ሸኮዎች ከጥንት ጀምሮ ዛሬም ድረስ የሚጠቀሙበት በጎ እሴታቸው ነው። በፍቅር የሚማግ ንጹህ አየር እና ኩልል ያሉ ምንጮች፣ ፏፏቴዎችና ክረምት ከበጋ የማይደርቁ ወንዞች ሕያው ምስክርና ሌላው የአካባቢው ድምቀቶች ናቸው። የቤንች ሸኮ ዞን ለምለም የተፈጥሮ ደን፤ ደን ብቻ ሳይሆን የኢኮኖሚ ምንጭም ጭምር ነው። መኖሪያ ቤቶችን የከበቡ ዛፎች የማንጎ፣ የብርቱካን፣ የፓፓያ፣ የአቮካዶ፣ የሙዝ፣ የእንሰት አሊያም ሌላ ለምግብነት የሚውሉ ናቸው። እምቅ የሆነው የተፈጥሮ ደን ደግሞ በውስጡ ቡና፣ ኮረሪማ፣ ጥምዝ እና ሌሎችንም ቅመማ ቅመሞችን ያቀፈ ነው። ይህ እምቅ የኢኮኖሚ አቅም ለአካባቢው ማኅበረሰብ አለኝታም ሆኑ እያገለገለ ይገኛል። ለዚህም የአካባቢው ነዋሪዎች ብዙ ጊዜ "ደን ሕይወታችን ነው" ሲሉ ይደመጣሉ። አዎ ደን ሕይወት ነው፣ ደን እስትንፋስ ነው፣ ደን ምግብና ውሃም ጭምር ነው። ትናንት የአንድ ጀንበር የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የተከናወነበት የሸኮ ወረዳ "አሞራ ገደል" የተባለ ድንቅ ተፈጥሯዊ ገጽታ አለው። አሞራ ገደል ጥቅጥቅ ባሉ ዕድሜ ጠገብ ዛፎች ከመከበቡ ባሻገር ከስር ወንዝ እያለፈ ከላይ ተሽከርካሪ የሚያልፍበትን በተለምዶ "የእግዜር ድልድይ" እየተባለ የሚጠራውን ግዙፍ ድልድይንም በውስጡ ይዟል። አረንጓዴ ካባ የደረበው ጋራ ሸንተረሩ ለዓይን የሚማርክ መስህብ ስፍራም ጭምር ነው። የደኑ ጫፍ ከ20 የሚበልጡ ፍል ውሃዎችን በአንድ ሰብስቦ በመያዙ በየእለቱ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ከደዌያቸው ለመፈወስ ሲሉ ወደስፍራው ይመጣሉ። ታዲያ በዚህ ደን ተከበው የሚኖሩ የአካባቢው አርሶ አደሮች ችግኝ ከመትከል አልቦዘኑም። ባላቸው ከመኩራራት ይልቅ ትርጉም ባለው መልኩ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወኑ ነው። ዛሬም በትጋት ችግኝ እየተከሉ ነው፤ ነገም ይቀጥላሉ። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከፍራፍሬ ባሻገር የነገን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት በማሰብ የቁንዶ በርበሬ ቅመም ለማልማት በማቀድ የግራቪላ ዛፍ ተከላ ላይ ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ ነው። ይህ እሳቤ ደን ውስጥ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ የሚያደርጋቸውን ችግኝ እንዲተክሉ እያደረጋቸው ነው። በደኑ ዙሪያ ያሉ ገላጣ ሜዳዎች በችግኝ እየተሞሉ ነው። የአርሶ አደሩ ማሳም በፍራፍሬ ተንበሽብሿል። በተለይ አካባቢው ለፍራፍሬ ምርት ያለው ተስማሚነት በአጭር ጊዜ ውስጥ ውጤታማ ስለሚያደርጋቸው በራሳቸው በቅለው በማደግ ላይ ያሉ የደን ዛፎችን አንስተው በፍራፍሬ ይተካሉ። ይህ ወቅቱ የሚጠይቀው ብልህነት የተሞላበት የልማት አርበኝነት ነው፤ የአካባቢውን ስነ ምህዳር እየጠበቁ በኢኮኖሚ የመበልጸግ ትልም ያለው ጉዞ ማሳያም ነው። በዚህም የቤንች ሸኮ ዞን ባለፉት ዓመታት በተተከሉ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራ በፍራፍሬ ዘርፍ ሰፊ ውጤት ከተመዘገበባቸው የክልሉ አካባቢዎች የሚጠቀስ ነው። ለአብነትም በደቡብ ቤንች ወረዳ ውስጥ የሚገኘው የጃንቹ ተራራ "የአረንጓዴ አሻራ ልማት ያከበረው ተራራ" መሆን ችሏል። ስፍራው ምንም እንኳ ፍጹም ገላጣ ባይሆንም ለእርሻ ሥራ የማይመች በመሆኑን ለዘመናት ጾሙን አድሯል። የአረንጓዴ አሻራ ልማት ከተጀመረ ወዲህ ሙሉ በመሉ የሙዝ ችግኝ ተተክሎበት ዛሬ ላይ የሙዝ ፍሬ የሚሰበሰብበት የኢኮኖሚ ማዕከል ሆኗል ማለት ይቻላል። ይህ ተሞክሮም የበርካቶችን ወኔ ቀስቅሶ በአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራ ላይ በራስ ተነሳሽነት እንዲዘምቱ ምክንያት ሆኗል። ክረምትን ብቻ ሳይጠብቁ የበልግ ወራትንም መደበኛ የችግኝ ተከላ ወቅት አድርገው ቡናን ጨምሮ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ ችግኞችን አርሶ አደሮቹ በማሳቸው በስፋት ይተክላሉ። በቤንች ሸኮ ዞን በደን ውስጥ ያረፈ አረንጓዴ አሻራ ዛሬ ምግብ ነው፤ ገንዘብም ነው። የዛሬ ሦስት ዓመት በዚሁ የአረንጓዴ አሻራ ያለሙት የሙዝ ችግኝ ለፍሬ መድረሱን ከተናገሩ አርሶ አደሮች መካከል የሸኮ ወረዳ ነዋሪው ሁሴን እንድሮ ተጠቃሽ ናቸው። ሙዝ ብቻ ሳይሆን የተከሉት የግራቪላ ችግኞች አድገው ከሥራቸው የተተከለው የቁንዶ በርበሬ ቅመም ተስፋ ሰጪ ቁመና ላይ ይገኛል ብለዋል። ከሁለት ዓመታት ወዲህ በአካባቢው የፍራፍሬ ምርት መጨመሩን የተናገሩት ደግሞ ወይዘሮ ምሳዬ መሐመድ ናቸው። ዋጋውም የተረጋጋ፣ አቅርቦቱም ከፍ ያለ መሆኑን አንስተዋል። ለዚህ ደግሞ የአረንጓዴ አሻራ ኢኒሼቲቭ ትልቅ ሚና እንደተጫወተ ነው የገለጹት። ይህን መነሻ ሆኗቸው እርሳቸውም ችግኝ በመትከል አሻራቸውን በማሳረፍ ላይ ናቸው። የቤንች ሸኮ ዞን ደን፣ አካባቢ ጥበቃና ኅብረት ሥራ መምሪያ ኃላፊ አቶ መስፍን ጉብላ እንደሚሉት በዞኑ ችግኝ የሚተከለው ገላጣ ቦታዎችን በመፈለግ ብቻ ሳይሆን ከጥቅጥቅ ደኖች ውጭ ያሉ የባህር ዛፍና ተጨማሪ ጥቅም የሌላቸውን ዛፎች በማንሳት ጭምር ነው። ለአብነትም የባህር ዛፍ ደንን አንስተው በቦታው የተተከለው ሙዝ የአፈር ለምነትን ከመጠበቅ ባሻገር ፍሬ በመስጠት የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና እያረጋገጠ ነው። በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ30 ሚሊዮን በላይ የፍራፍሬ ችግኞችን በመትከል የማሳ ሽፋኑን ለማሳደግ ታልሞ እየተሠራ መሆኑንም ጠቅሰዋል። አቶ መስፍን እንዳሉት ከአምስት ዓመታት በፊት በዞኑ የነበረው 29 ሺህ ሄክታር የፍራፍሬ ማሳ ዛሬ ላይ ወደ 100 ሺህ ሄክታር ማሳ አድጓል። ይህም በየቀኑ በርካታ ተሽከርካሪዎች ከዞኑ ወደ ማዕከላዊ ገበያ የፍራፍሬ ምርት ጭነው እንዲወጡ እያስቻለ ነው። በዚህም ተጨባጭ ውጤት የአርሶ አደሩ ኑሮ እና የዞኑ ኢኮኖሚ እያደገ መምጣቱን አቶ መስፍን ይገልጻሉ። የቤንች ሸኮዎችን ተሞክሮ ያነሳንበት ዋና ዓላማ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከአካባቢ ጥበቃ እና ደን ልማት ያለፈ አንድምታ እንዳለው ለማሳየት ነው። ደን አለን ብለው በመኩራራት ያልተቀመጡ የቤንች ሸኮ እጆች ዛሬ የልማት ትሩፋታቸውን እየለቀሙ ነው። በመትከል መመገብ፣ በመትከል ሀብትን ማካበት፣ በመትከል ከድኅነት ወደ ራስን መቻል ማንሠራራት እንደሚቻል የእነሱ ልምድ ለብዙዎች ተሞክሮ ይሆናል። ሰላም!
ለለውጥና ስኬት የሚታትሩ እጆች
Jul 28, 2025 462
(በማሙሽ ጋረደው) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሆሳዕና ከተማ የሚኖረው ወጣት ሀብታሙ ደስታ፤ የአንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አጠናቆ ወደ ከፍተኛ ትምህርት በመግባት የመጀመሪያ ዲግሪውን በቢዝነስ ማኔጅመንት ተመርቋል። ሀብታሙ ከተመረቀበት ሙያ ባሻገር በአካባቢው መልካም እድሎችን በማጥናት ሰርቶ ለመለወጥና አግኝቶ ለማደግ ወሰነ። በዚህም መሰረት የቤትና የቢሮ ዕቃዎች ከሚያመርት አንድ የግል ድርጅት ውስጥ በመቀጠር ስራ ጀመረ። በድርጅቱ ውስጥ እየሰራ እና የሙያ ክህሎቱን እያሳደገ በሙያው የላቀ ብቃት እያካበተ መምጣቱን ያስታውሳል። በዚህም መሰረት ከሰባት ዓመት በፊት ከጓደኞቹ ጋር በመደራጀት በ70 ሺህ ብር መነሻ ካፒታል በተመሳሳይ የእንጨት ስራ ጀመረ። በ70 ሺህ ብር የተጀመረው ስራም አሁን ላይ ካፒታሉ 10 ሚሊዮን ብር የደረሰ ሲሆን ከ40 ለሚልቁ ወጣቶችም የስራ እድል የፈጠረ ሆኗል። በሀገራችን የተለያዩ እድሎችና የስራ አማራጮች አሉ የሚለው ሀብታሙ፤ አንዳንዶች ስደትን የመጨረሻ አማራጭ ከማድረግ ይልቅ በየአካባቢያቸው ሰርቶ የመለወጥ እድል መኖሩን ማየት አለባቸው ሲል ተናግሯል። በአካባቢው ሰርቶ መለወጥ የሚያስችሉ በርካታ ዕድሎች መኖራቸውን አንስቶ እርሱ የተሰማራበት የእንጨት ስራ ሁነኛ ማሳያ መሆኑንም ጠቅሷል። የሀብታሙ ለለውጥና ስኬት የሚታትሩ እጆች ዛሬ ላይ ከራሱ አልፎ ለሌሎች የስራ ዕድል መፍጠር አስችለዋል። ለመለወጥ ቁርጠኝነትና ጠንክሮ መስራት የግድ መሆኑን የሚናገረው ወጣቱ ተስፈኛ "ያለጥረት የሚገኝ ስኬት የለም" ሲልም ተናግሯል። የሚያመርቷቸው የቤትና የቢሮ ዕቃዎች በብዙዎች ዘንድ ተፈላጊ መሆናቸውን አንስቶ የራሱ እና የጓደኞቹ እንዲሁም የሌሎች የኑሮ ሁኔታ እየተቀየረ መሆኑን ገልጿል። በተለይም ወጣቶች በአካባቢያችን ያሉንን በርካታ አማራጮች ለይተን የማየትና የመጠቀም ውስንነቶቻችንን ማረም ከቻልን ከራሳችን አልፈን ለሌሎች መትረፍ የምንችልበት ምህዳር ተፈጥሯል፡፡'' ብሏል። በከምባታ ዞን አዲሎ ዙሪያ ወረዳ ጆሬ ቀበሌ የሚኖሩት ሞዴል አርሶ አደር ሰለሞን ወልዴ፤ የጤና እክል ገጥሟቸውም ቢሆን እየታገሉ ከመስራትና ማምረት አልቦዘኑም። የህይወት መንገድ ብዙ ውጣ ውረድ የሚጠይቅ በመሆኑ ባለመስነፍና ተስፋ ባለመቁረጥ መስራት ይገባል የሚል እምነት አላቸው። በመሆኑም የእርሻ ስራ እና የዶሮ እርባታን ጭምር በማቀናጀት ከራሳቸውና ቤተሰባቸው የምግብ ዋስትና አልፈው ለሌሎችም የሚተርፍ ስራ እያከናወኑ ይገኛሉ። በመሆኑም በተለይ እምቅ ችሎታና ያልደከመ ጉልበት ያላቸው በመሆኑ በተለያዩ የልማት መስኮች መልፋት፣ መስራትና ውጤት ማምጣት እንዳለባቸው ይመክራሉ። የኢትዮጵያ አየር ለመኖር የተመቸ፤ ለማምረት ተስማሚ በመሆኑ እድሉን ተጠቅሞ በቀላሉ ማደግና መለወጥ የሚቻል መሆኑን አንስተዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የስራ እድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሙስጠፋ ኢሳ፤ በክልሉ ያለውን እምቅ ኃብት በማልማትና በማምረት ከተረጂነት ወደ አምራችነት ለመሸጋገር ሰፊ ጥረት እየተደረገ ስለመሆኑ ተናግረዋል።በመሆኑም በተለይም ወጣቶች የመስራትና የፈጠራ ችሎታቸውን ተጠቅመው የሀገር ልማትና እድገት መሪ ተሰላፊ እንዲሆኑ ጠይቀዋል። በክልሉ የስራ ዕድል የፈጠሩና የውጭ ምንዛሪ ወጪን የቀነሱ ኢንተርፕራይዞች መፈጠራቸውን አንስተው በመንግስት የብድር አቅርቦት፣ የግንዛቤና የህይወት ክህሎት ስልጠናን በመስጠት እገዛ የሚደረግ መሆኑንም አረጋግጠዋል። በክልሉ በ2017 በጀት ዓመት በግብርናና በኢንዱስትሪ ዘርፍ ብቻ ከ370 ሺህ ለሚልቁ ዜጎች የስራ እድል መፈጠሩን አስታውሰው በተያዘው በጀት ዓመት ደግሞ ለ400 ሺህ ሰዎች ስራ ለመፍጠር ታቅዷል ብለዋል።
የመስቀሎ ቀበሌዋ "ግቢው መንደር"
Jul 25, 2025 450
ሰቆጣ፤ሐምሌ 18/2017(ኢዜአ)፡- የመስቀሎዋ ግቢው መንደር "የነባር ደኖች ባለጸጋ፤ የአረንጓዴ ልማት መገለጫ" "ግቢው መንደር" ከርቀት ሲመለከቷት እድሜ ጠገብና አዳዲስ የለሙ ደኖችን የያዘች በልምላሜዋ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየታወቀች የመጣች፤ አርዓያነቷም እየገነነ የመጣ ትንሽዬ መንደር ናት። የእድሜ ጠገብ ደን ባለቤትና የአዳዲስ ደን ልማት መገለጫ የሆነችው "ግቢው መንደር" የምትገኘው ዝናብ አጠር በሆነውና የተራቆተ ተራራ አግጦ በሚታይበት በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በጋዝጊብላ ወረዳ መስቀሎ ቀበሌ ነው። ግቢው መንደር በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ትልቁ ተራራ በሆነው ቤላ ተራራ ስር ከተመሰረቱ መንደሮች አንዷ ናት። ግቢው መንደር መቼና እንዴት እንደተመሰረተች በታሪክ ተሰንዶ በብእር የተከተበ ሰነድ ባይገኝም የዋግ ሹማምንት እንደ መሰረቷት ይነገራል። ከዋግ ሹማምንት የተወሰኑ ባላባቶች በመንደሯ ይኖሩ እንደነበርና ለስራ ባቀኑባቸው የኢትዮጵያ ክፍሎች ሁሉ የተለያዩ የዛፍና የአትክልት ዝርያዎችን ይዘው በመምጣት በቤታቸው ጓሮ ይተክሉ እና ዝርያውንም ለሃገሬው ማህበረሰብ ያስተዋውቁ እንደነበር የቀኝ አዝማች ሃይሉ ክንፉ ልጅ የሆኑት አቶ ሃብተ ማርያም ሃይሉ ይናገራሉ። እንዲየውም ይላሉ አቶ ሃብተ ማርያም ‘’ከአባቴ የባህር ዛፍ እንጨት የሚለምን ከመጣ የባህር ዛፍ ችግኝ ወስዶ አሳድጎ እንዲመልስ ይደረግ ነበር’’ ብለዋል። ‘’ለዛም ነው በግቢው መንደር ለእፅዋት ልዩ ትኩረት የሚሰጠው እና እድሜ ጠገብ ዛፎች የሚበዙት’’ ሲሉም አስረድተዋል። የአሁኑ ትውልድም ለእፅዋት ልዩ ትኩረት በመስጠት የአካባቢውን የቀደመ ልምላሜ ይበልጥ ለማጠናከር እየተጋ መሆኑንም አክለው ተናግረዋል። ነባሩን ደን በመንከባከብና በመጠበቅ፣ አዳዲስ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውና ነባር የደን ችግኞችን በመትከልና በማልማት የአካባቢያቸውን ገጽታ የመቀየርን አደራ የተረከቡ ነዋሪዎች መገኛ ነው "ግቢው መንደር"። ለዚህ መንደር አረንጓዴ መልበስ፣ ውብና ማራኪ መሆን ደግሞ እንደ አርሶ አደር ወንድሙ ሃይሉ ያሉ ታታሪ የመንደሯ ነዋሪዎች የስራ ትጋት በግንባር ቀደምትነት ይነሳል። አርሶ አደር ወንድሙ ሃይሉ ስለመንደሯ ሲያብራሩ ‘’በጊቢው መንደር ፆም የሚያድር መሬት የለም‘’ በማለት ይጀምራሉ፡፡ ተራራዎቿ በባህር ዛፍ ፅድ፣ በወይራና በሌሎች ነባርና አዳዲስ ደኖች መሸፈናቸውን በማስረገጥ ሃሳባቸውን ያጠናክራሉ። የመንደሯ ሸለቆዎችና የእርሻ መሬቷ ደግሞ ዓመቱን ሙሉ ጥቅል ጎመን፣ ድንች፣ ሽንኩርትና ሌሎች አትክልቶችና ፍራፍሬዎች የሚመረቱባት የበለጸገች መንደር እንደሆነችም ይገልጻሉ። ‘’በመንደሯ ያሉ እድሜ ጠገብ ዛፎች ከቀደምት አባቶቻችን የወረስናቸው የልምላሜ መገለጫዎች ከመሆናቸውም ባለፈ አባቶቻችን ለእፅዋት ያላቸውን ክብር ማረጋገጫ ናቸው።’’ በማለት ‘’የበለጠ በመጠበቅና በማልማት ከአባቶቻችን የወረስውን የአካባቢ ልምላሜ ለልጆቻችን ለማውረስ እየተጋን ነው’’ ብለዋል። አርሶ አደሩ በመኖሪያ መንደራቸው አካባቢ ያሉ ነባር ደኖችን ከመንከባከብ ባሻገር የተራቆተውን መሬት ተንከባክበው ሶስት ሺህ የባህር ዛፍ ደን እያለሙ እንደሚገኙም ተናግረዋል። በተያዘው የክረምት ወራትም ሁለት ሺህ ችግኞችን ለመትከል አቅደው ስራ መጀመራቸውን የገለፁት አርሶ አደር ወንድሙ የአካባቢያቸው ልምላሜ አሁን ካለበት ወደ ላቀ ደረጃ እስኪሸጋገር የአረንጓዴ ልማት ስራቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልፀዋል። ‘’ሁሉም የመንደራችን ነዋሪ ለእፅዋት ትልቅ ክብር ያለው በመሆኑ ተተኪው ትውልድም አርዓያውን እንዲከተል ትምህርት እየሰጠን እንገኛለን።’’ ብለዋል። የአርሶ አደር ወንድሙ ሃይሉ ልጅ የሆነው ወጣት አበባው ወንድሙ በበኩሉ በመንደራቸው ያለውን ልምላሜ ለማስፋት በግልና በማህበር ተደራጅው እስከ አምስት መቶ ዛፍ ተክለው እየተንከባከቡ መሆኑን ገልጿል። ‘’የጀመርነውን ተግባር በቀጣይ አጠናክረን ለማስቀጠል በተያዘው ክረምት ተጨማሪ ችግኞችን በመትከል የአባቶቻችንን ፈለግ ተከትለን አካባቢያችን በአረንጓዴ አሻራ ልማት ታዋቂ እንድትሆን እየሰራን እንገኛለን’’ ብሏል። የመስቀሎ ቀበሌ ሊቀ መንበር አቶ ታዴ ጌታሁን በበኩላቸው ግቢው መንደር በአረንጓዴና በመስኖ ልማት ስራ ከቀበሌያቸው ሞዴል መንደር መሆኑን አመልክተዋል። ሌሎች የቀበሌያቸው መንደሮችም ከግቢው ተሞክሮና ልምድ በመውሰድ በአረንጓዴ ልማት ከፍተኛ መነቃቃት እያሳዩ ነው ያሉት አቶ ታዴ ተሞክሮውን በመውሰድ በቀበሌያቸው እፅዋትን መቁረጥና ማውደም እንደነውር የሚቆጠርበት ስርዓት ለመፍጠር እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ሞገስ ሃይሌ እንዳሉት የግቢው መንደር አርሶ አደር በአረንጓዴ ልማት ከመሳተፍ ባሻገር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱ እያደገ መጥቷል ብለዋል። ዓመቱን ሙሉ አረንጓዴ አትክልትና ፍራፍሬ የሚመረትባት መንደሯ የሷን ተሞክሮ ወደ ደብረ ወይላ፣ ዛሮታ፣ ሲልዳና ኒሯቅ ቀበሌዎች በማስፋት ቀጠናውን የአረንጓዴ ልማት መገለጫ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝም አመልክተዋል።
ውሎህ አንተነትህን ይወስነዋል!!!
Jul 24, 2025 345
ወላጆቻችን ዘወትር ጠዋት ወደ ስራቸው ከመሰማራታቸው ወይም ከቁርስ በፊት “አማን አውለን፤ ውሏችንን አሳምርልን፤” ብለው ፈጣሪያቸውን ይለምናሉ፡፡ ውሎ ለሰው ልጅ መሰረታዊ ነገር ነው፡፡የሰውን ልጅ አካላዊ፣ መንፈሳዊ እና ቁሳዊ እድገት ይወስናል፤ ማንነትንና አስተሳሰብን ይቀርፃል፡፡ይህ በበኩሉ የምንኖርበትን አውድ ይፈጥራል፡፡ አውዱ በጎም፣ መጥፎም ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ የሚወሰነው በተቀረጽክበት እሳቤ ነው፡፡ ይህን ጉዳይ በፖለቲካው አውድ ከፍ አድርገን ካየነው ተመሳሳይ ሁኔታን እናገኛለን፡፡ በፖለቲካዊ ሁኔታዎች ውስጥ የሰው ልጅ ባህሪ በምክንያታዊነት ወይም ግላዊ ሁኔታ ብቻ አይወሰንም። ይልቁንም በማህበራዊ ግንኙነትና እሱ በሚፈጥረው ካባቢያዊ አውድ መስተጋብር ጭምር ነው፡፡ “ጠብ መንጃ” አንጋቾችም ይሁኑ ቆሞ ቀር ፖለቲከኞች፣ ባንዳዎች እና አጫፋሪዎቻቸው ለምንድን ነው ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ከሌላው በተለየ ሁኔታ ነጥለው ማጥቃት የሚፈልጉት? የሚለውን ጥያቄ ካየን፣ ጉዳዩ ከውሎ ጋር የተገናኘ ነው፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ውሎ አረንጓዴ አሻራ ለማኖር ጫካ ነው። የስንዴ፣ የሩዝ፣ የቡና፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ማሳ ነው። የኮሪደር ልማት፣ የሌማት ትሩፋት እና የኢንዱስትሪ መንደር ነው። የኢትዮጵያን ፀጋዎች አሳሳ ነው። እሳቸው በውሏቸው ያሉንን ፀጋዎች መለየት ብቻ ሳይሆን ፀጋዎቹ ወደ ተጨባጭ ውጤት እንዳይቀየሩ ያደረጉትን መሰረታዊ ችግሮች መለየት እና መፍትሄዎቻቸውን ማስቀመጥ ነው። በአይነ ህሊናቸው በጸጋዎች ውስጥ ሆኖ የተጎሳቆሉና የቆሸሹ መንደሮች፣ አካባቢዎች እና በዚህ ውስጥ የሚኖሩ ዜጎችን በመመልከት የመውጫ መንገዱን በቁጭት ማለም ነው። ያለሙትን ወደ ተጨባጭ እቅድ ለውጠው በተግባር ወደ ውጤት መቀየር ነው። በእሳቤያቸው እና በዕቅዱ ላይ በዙሪያቸው ያሉትን አመራሮች፣ የፓርቲውን አባላት፣ ቅን ዜጎችን በማስረዳትና በማስተባበር ወደ ተጨባጭ ተግባር ይቀይሩታል። ህዝቡንም ባለሃብቱንም በማቀናጀት ይበልጥ ውጤታማ ያደርጉታል። በዚህም ማንም ሊክደው በማይችል መልኩ መንደሮች፣ አካባቢዎች፣ ከተሞች እየተቀየሩ ነው። ዜጎች ጥሪት እያፈሩ ነው። ኢኮኖሚው እያደገ ነው። ብቁ ተቋማት እየተገነቡ ነው። ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ እመርታ እየታየ ነው። ኢትዮጵያም እያንሰራራች ነው፡፡ ሀቁ ይሄው ነው። እኛ ኢትዮጵያውን ብቻ ሳንሆን የሌሎች ሀገራትና የዓለም አቀፍ ተቋማት መሪዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ ቱሪስቶች እያደነቁት ነው፡፡ አንዳንዶቹም ልምድ ከኢትዮጵያ እያቀሰሙ ነው፡፡ የኮንፈረንስ ቱሪዝም እየጎረፈ ነው፡፡ ይህ የውሎ ውጤት ነው፡፡ የስኬቱ ምንጭም በውሎው በተፈጠረው አውድ ላይ የተደረገ ቁርጠኛ ርብርብ ነው፡፡ ፈጣሪ የሰጠህን እውቀት፣ ክህሎት እና ፀጋ ለለውጥ፣ እድገትና ለብልጽግና መጠቀም በሚያስችል አውድ ላይ ውሎህን ከመሰረትክ በእርግጥም ስኬታማ ትሆናለህ፡፡ ውሎህን የሴራ ፖለቲካ፣ በአቋራጭ ወደ ስልጣን በመምጣት ግለሰባዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ፣ ቆሞ ቀር የጽንፍና የጥላቻ አስተሳሳብ የተጠናወተው አውድ ውስጥ ካደረግከው አስተሳሰብህንና እይታህን የሚቀርጽህ፣ ማንነትህንም የሚበይነው እና ድርጊትህን የሚወስነው ይህ አውድ ነዉ፡፡ ይህ አውድ ባሪያው ያደርግሃል፡፡ “ማር ለአህያ አይጥማትም” እንደሚባለው ዓለምን ጉድ ያሰኘ ተዓምር ቢፈጠር አይጥምህም፡፡ እንደ ኮሶ ይመርሃል፡፡ያንገፈግፈሃል፡፡ ያንገሸግሽሃል። ከዚህ አውድ መላቀቅ የምትችለው ሩቅ አላሚ፣ ወገንህን ተመልካች፣ የአንድን አካባቢ ወይም ሀገር መሠረታዊ ችግሮች ሳይንሳዊና ጥባባዊ መርህና ህጎች በመከተል እና በብቃት በመለየት ተግባራዊ የመፍትሄ ሃሳብ ማፍለቅ ስትችል ነው፡፡ ጠብ መንጃ አንጋቾች፣ ቆሞ ቀር ፖለቲከኞች፣ ባንዳዎች እና አጫፋሪዎቻቸው ማድረግ ያልቻሉት ጉዳይ ይህን ነው፡፡ ምክንያቱም ውሎአቸውና እሱ የፈጠረው አውድ ይህን ማድረግ አይፈቅድላቸውም፡፡ ይህ እንዲነሳባቸው አይፈልጉም፡፡ ሰነፎችና ርዕይ አልባ ስለሆኑ፣ ሞክረውትም ስለማያውቁ ይኮሰኩሳቸዋል፡፡ ስለሆነም እንደ መፍትሔ የሚወስዱት የበጉን እረኛ ከበጎቹ ነጥሎ መምታት ነው፡፡ ከዚያም በጎቹን እንደፈለጉ ማድረግ ነው፡፡ ይህ የቅዠትና የምናብ መፍትሄም ከውሎአቸው የሚቀዳ ነው፡፡ ያልተረዱት ነገር እረኛው በጎቹን እንዴት መጠበቅ እንዳለበት ጠንቅቆ ማወቁን ነው፡፡ በጎቹም ቢሆኑ እረኛቸውን ላያስነኩ ምለው መገዘታቸውን ነው። እነዚህ በውሎ አውዳቸው ምክንያት የቅዠት እስረኞች የሆኑ ባንዳዎች ይህ ምሳሌያዊ ንግግር እንኳ በእውናዊው ዓለም ስላሉ “በጎችና እረኛ” የተፃፈ ይመስላቸው ይሆናል። እናም ወዳጄ፣ ውሎህ እይታህን እንኳ ይወስነዋል፤ መፍትሔውም ውሎህን መምረጥ ወይም ማስተካከል ነው፡፡ አሁን አሁን ደግሞ “ከዐቢይ በኋላ” የሚባል ዲስኩርም እየሰማን ነው፡፡ ይሄም የውሎ ውጤት ነው፡፡ የበርካታ አስርት ዓመታት ቆሞ ቀር የፖለቲካ እሳቤ የወለደው የ“ሽግግር መንግስት መዝሙር” አውድ የፈጠረው ነው፡፡ አውዱ ውስጥ ያለው እሳቤ ቆሞ ቀር ግትር እሳቤ ነዋ!! ወዳጄ ጭንቅ አይግባህ! ከዐቢይ በኋላማ ዐቢይ እራሱ ሀገሩን ለትውልድ ትውልዱን ለሀገር እያዘጋጀ ነው፡፡ ይህ እውነት መሆኑን እንዳትክድ ያለፉትን ሰባት ዓመታት እመርታዎች ተመልከት፤ ምን እንደተሰራ ቆጥሬ አልጨርስልህም። ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የወያኔ ሰዎች ተገቢ ያልሆነ እንቅስቃሴን አጢነው ሰሞኑን አንድ ምጥን መልዕክት አስተላልፈው ነበር፡፡ “ያለፈውም ለማንም አልበጀ፣ አካባቢውንም ሀገርንም አልጠቀመም፤ትርፉ ኪሳራ ነበር፡፡ ወደ ግጭት ለመግባት የሚደረገው ሙከራ ሌላ ጉዳት ያመጣ ይሆናል እንጂ አይጠቅምም፡፡ ጥያቄያቹሁን በሰለጠነ አግባብና በህገ መንግስቱ መሠረት ጠይቁ፡፡ ተዉ የሚል መልዕክት፡፡” ይህን ተከትሎ በጠብ መንጃ አንጋቾች፣ ቆሞ ቀር ፖለቲከኞች፣ ባንዳዎች እና አጫፋሪዎቻቸው ሰፈርና መንደር ጩኸት በረከተ፡፡ ለምን? በዚያ መንደር ያለው አውድ ሰላም፣ ልማት፣ ብልጽግና፣ ከልመና መውጣት፣ ስንዴ፣ የሌማት ቱሩፋት…ወዘተ አጀንዳ አይደለማ!! በዚያ አውድ ትርፍ የሚገኘው ከግጭት ነው፡፡ ህግ እና ስርዓት ባለበት ወርቅ መዝረፍ አትችልማ!! የማርሻሉ አውድ ደግሞ አስተማማኝ የመከላከል፣ ብሔራዊ ጥቅም የማስከበር፣ የፌዴራል ስርዓቱ ጠባቂ እና የዜጎች ጥቅምና ደህንነት አስከባሪ ሰራዊት መገንባትን እንጂ መንደርተኝነትን የሚቀበል አይደለም፡፡ ይህ የውሎ ጉዳይ በማህበረሰቡ ውስጥም በተለያየ ሁኔታ ይገለፃል፤ ሰሞኑን የኪነጥበቡ ዓለም አንዱ አውድና መገለጫ በሆነው በሙዚቃ ኢንደስትሪው፣ ሙያተኞችን ነጥሎ የመምታት አባዜም የዚሁ የውሎ ጉዳይ ነው። ውሎህ አንተነትህን ይወስነዋል የሚባለው ለዚሁ ነው!! ለገሰ ቱሉ(ዶ/ር) የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር
የሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ በምን ጉዳዮች ላይ ይመክራል?
Jul 21, 2025 430
ሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ ከሐምሌ 20 እስከ 22 ቀን 2017 ዓ.ም በኢትዮጵያ አዲስ አበባ ይካሄዳል። የስርዓተ ምግብ ጉባኤው በሐምሌ ወር 2015 ዓ.ም በጣልያን ሮም የተካሄደው የመጀመሪያ የተመድ ስርዓት ምግብ ላይ የተገቡ ቃሎች ትግበራ ሂደትን መነሻ በማድረግ የሚካሄድ ነው። ቀዳሚ ትኩረቱ ከመጀመሪያው ጉባኤው በኋላ የምግብ ስርዓትን አስመልክቶ ያሉ ለውጦች ምንድን ናቸው? የሚለው ነው። በጉባኤው ላይ ሀገራት የምግብ ስርዓት ትራንስፎርሜሽንን አስመልክቶ ያገኟቸውን ስኬቶች እና ያጋጠሟቸው ተግዳሮቶች ላይ ሪፖርት ያቀርባሉ። በተለይም የምግብ ስርዓት ሽግግሩ ሁለንተናዊነት እና ሁሉን አሳታፊነት ዋንኛ ትኩረት የሚሰጠው ጉዳይ ነው። ሁለተኛው የጉባኤው አጀንዳ በመንግስታት፣ የምግብ አምራቾች፣ የንግድ ማህበረሰቡ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት መካከል ያለውን አጋርነት ማጠናከር ነው። የባለድርሻ አካላት ትብብር መጠናከር የምግብ ስርዓት ትራንስፎርሜሽንን ለማሳካት ቁልፍ ሚና እንዳለው ታምኖበታል። በተጨማሪም ሀገራት እና ተቋማት በሮሙ ጉባኤ የገቧቸው ቃሎች የደረሱበትን ደረጃ የሚገመገም ሲሆን ቀጣይ አቅጣጫዎች ይቀመጣሉ ተብሎም ይጠበቃል። ለምግብ ስርዓት ሽግግር የፋይናንስ አማራጮችን ማስፋት እና የኢንቨስትመንት መጠንን መጨመር በሚቻልበት ሁኔታ ላይም ጉባኤው ይመክራል። ለምግብ ስርዓት ሽግግር ስራዎች በአነስተኛ ወለድ የፋይናንስ አቅርቦትን ተደራሽ ማድረግ፣ አማራጭ የፋይናንስ ምንጮችን መጠቀም እና ሀገር በቀል የፋይናንስ መሰብሰብ አቅምን ማጎልበት ላይ ምክክሮች ይደረጋሉ ። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ በሮም በነበረው ጉባኤው ላይ ይፋ ያደረጓቸው ስድስት የትኩረት መስኮች አፈጻጸም ግምገማ ሌላኛው አጀንዳ ነው። በአፍሪካ መዲናዋ አዲስ አበባ የሚካሄደው ሁለተኛው የተመድ የስርዓተ ምግብ ጉባኤ የሀገራት መሪዎች እና ተወካዮች፣ ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ አርሶ አደሮች፣ አምራቾች እና የምግብ ስርዓት ሽግግር ተዋንያንን በአንድ መድረክ የሚያገናኝ ነው። በጉባኤው ላይ ከዋናው ሁነት ጎን ለጎን የምግብ ስርዓት ትራስፎርሜሽን እና የስርዓተ ምግብ ሽግግርን አስመልክቶ 31 የጎንዮሽ ስብስባዎች ይደረጋሉ። ከጎንዮሽ ስብስባዎቹ ሁለቱ ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በመሆን በስርዓተ ምግብ ትራንስፎርሜሽን እና እንስሳት ጤና ጥበቃ ጉዳዮች ያዘጋጀቻቸው ናቸው። ኢትዮጵያ በምግብ ስርዓት ሽግግር ያከናወናቸውን ስራዎች አስመልክቶም በጉባኤው ተሳታፊዎች የመስክ ምልከታ ይደረጋል። ኢትዮጵያ በስርዓት ምግብ ትራንስፎርሜሽን፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ እና በግብርናው ዘርፍ ባደረጋቻቸው ሀገር በቀል ሪፎርሞች ያስመዘገበቻቸው ውጤቶች ጉባኤውን እንድታስተናግድ የተመረጥችባቸው ምክንያቶች ናቸው።
ከሮም እስከ አዲስ አበባ
Jul 11, 2025 764
ሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ ከሐምሌ 20 እስከ 22 ቀን 2017 ዓ.ም በኢትዮጵያ አዲስ አበባ ይካሔዳል። የምግብ ስርዓት ትራንስፎርሜሽን ኢንቨስትመንት እና ፋይናንስ፣ የምግብ ስርዓት ሽግግር ሁለንተናዊነትና የተገቡ ቃሎችን ከመፈጸም አንጻር ያለውን የተጠያቂነት ስርዓት ማጠናከር ጉባኤው ትኩረት ያሚያደርግባቸው ሀሳቦች ናቸው። ሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተምግብ ጉባኤ በሐምሌ ወር 2015 ዓ.ም በጣልያን ሮም የተካሄደው የመጀመሪያ የተመድ ስርዓት ምግብ ላይ የተገቡ ቃሎች ትግበራ ሂደትን መነሻ በማድረግ የሚካሄድ ነው። በመጀመሪያው ጉባኤ ላይ የ182 ሀገራት ተወካዮች፣ 21 የሀገራት መሪዎች እና 126 ሚኒስትሮችን ጨምሮ 3 ሺህ 300 ተሳታፊዎች ታድመውበታል። በጉባኤው ላይ የተመድ ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ሀገራት እና ተቋማት ሊተገብሯቸው የሚገቡ ስድስት የትኩረት አቅጣጫዎችን ይፋ አድርገው ነበር። የምግብ ስርዓት ስትራቴጂዎችን ከብሄራዊ ፖሊሲዎች ጋር ማስተሳሰር፣ ሁሉን አቀፍ የምግብ ስርዓት አስተዳደር መገንባት፣ በጥናት፣ ዳታ፣ ኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ላይ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ፣ ሁሉን አቀፍ የእቅድ ዝግጅት እና ትግበራን ማጠናከር፣ በምግብ ስርዓት ውስጥ የንግዱ ማህበረሰብ ያለውን ድርሻ ማሳደግ እና የአጭርና የረጅም ጊዜ የአነስተኛ ወለድ የፋይናንስ አቅርቦትን ተደራሽ ማድረግ ከትኩረት አቅጣጫዎቹ መካከል ይጠቀሳሉ። ኢንቨስትመንት፣ የበጀት ድጋፍ እና የእዳ አስተዳደር ሌላኛው የትኩረት መስክ ነው። በጉባኤው ላይ 300 ገደማ በሚሆኑ ጉዳዮች ላይ በመወያየት የምግብ ስርዓት ሽግግርን እውን ለማድረግ ቃል መግባታቸውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት መረጃ ያመለክታል። በተለይም እ.አ.አ 2030 የማይበገር፣ ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ የምግብ ስርዓት መገንባት እንዲሁም ምግብ ለሁሉም የሚለውን ግብ ለማሳካት ጥረት እንደሚያደርጉ ሀገራት ቃል ገብተዋል። ሁሉን አሳታፊ ነው በሚል አድናቆት ያገኘው ጉባኤው በስርዓት ምግብ ላይ ግንዛቤን ከማሳደግ እና አቅምን ከመገንባት አንጻር ውጤታማ እንደነበር ይነሳል። የምግብ ስርዓት ሽግግር አንገብጋቢና ጊዜ የማይሰጥ ጉዳይ እንደሆነም በጉባኤው ተወስቷል። ኢትዮጵያም በስርዓተ-ምግብ ጉባኤው ላይ የነበራት ተሳትፎ ስኬታማ ነበር። በግብርናው ዘርፍ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ውጤታማ እንቅስቃሴዎችን የሚያሳዩ ልምደችን አቅርባለች። በጉባኤው ላይ የተገኙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢትዮጵያ ግብርናን በማዘመን የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥና በስርዓተ ምግብ ሽግግር ለማምጣት እየወሰደች ባለው የፖሊሲ እርምጃና ውጤቶች ዙሪያ ገለጻ አድርገውም ነበር። ኢትዮጵያ የኩታ ገጠም እርሻን በማስፋፋት፣ ለየስነ ምህዳሩ ተስማሚ የሆኑ የተሻሻሉ ዝርያዎችን፣ አነስተኛ ቴክኖሎጂዎችንና ሌሎች ግብአቶችን ለአርሶ አደሩ በማቅረብ የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ለኢኮኖሚው ዕድገት የላቀ አበርክቶ እንዲኖረው እየሰራች መሆኑንም አንስተዋል። በአረንጓዴ አሻራ፣ በበጋ መስኖ በተለይም በበጋ ስንዴ ምርት እና በሌማት ትሩፋት እየተገኙ ያሉ ውጤቶችን ለጉባኤው አቅርበዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በግብርና ዘርፍ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የስራ እድል ፈጠራን ለማበረታታትም ሆነ በስርዓተ-ምግብ ሽግግር ለማድረግ አዲስና የተለየ የፋይናንስ ሞዴል ያስፋልጋል በማለት በአጽንኦት ተናግረዋል። ዘላቂና አካታች የስርዓተ ምግብ ሽግግር አቅጣጫዎች ጥሩ አፈጻጸም የታየባቸው ቢሆንም በፋይናንስ አቅርቦት፣ በዓለም አቀፍ ትብብር፣ በአየር ንብረት ለውጥና በሰው ሰራሽ ምክንያት የሚፈጠሩ ችግሮችን ለመቋቋም በትብብር በመስራት በኩል በርካታ ችግሮች መስተዋላቸውን ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ የገለጹት። በመሆኑም ሀገሮች በስርዓተ ምግብ ላይ የሚታዩ ችግሮችን ለመቅረፍ በአነስተኛ እርሻ ስር-ነቀል ለውጥ በማምጣት ሽግግሩን ማፋጠን እንደሚገባቸው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአፅንኦት አንስተዋል። ለዚህም የሴቶችና የወጣቶች ተሳትፎን እንዲያሳድጉና ለግብርና ቴክኖሎጂ መስፋፋት እንዲሰሩ ጠይቀዋል ። ሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ-ምግብ ጉባኤ የመጀመሪያውን ጉባኤ መነሻ በማድረግ በተለያዩ አጀንዳዎች ይመክራል። ቀዳሚ ትኩረቱ ከመጀመሪያው ጉባኤው በኋላ የምግብ ስርዓትን አስመለክቶ ያሉ ለውጦች ምንድን ናቸው? የሚለው ነው። በጉባኤው ላይ ሀገራት የምግብ ስርዓት ትራንስፎርሜሽንን አስመልክቶ ያገኟቸውን ስኬቶች እና የጋጠሟቸው ተግዳሮቶች ላይ ሪፖርት ያቀርባሉ። በተለይም የምግብ ስርዓት ሽግግሩ ሁለንተናዊነት እና ሁሉን አሳታፊነት ዋንኛ ትኩረት የሚሰጠው ጉዳይ ነው። ሁለተኛው የጉባኤው አጀንዳ በመንግስታት፣ የምግብ አምራቾች፣ የንግድ ማህበረሰቡ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት መካከል ያለውን አጋርነት ማጠናከር ነው። የባለድርሻ አካላት ትብብር መጠናከር የምግብ ስርዓት ትራንስፎርሜሽንን ለማሳካት ቁልፍ ሚና እንዳለው ታምኖበታል። በተጨማሪም ሀገራት እና ተቋማት በሮሙ ጉባኤ የገቧቸው ቃሎች የደረሱበትን ደረጃ የሚገመገም ሲሆን ቀጣይ አቅጣጫዎች ይቀመጣሉ ተብሎም ይጠበቃል። ለምግብ ስርዓት ሽግግር የፋይናንስ አማራጮችን ማስፋት እና የኢንቨስትመንት መጠንን መጨመር በሚቻልበት ሁኔታ ላይም ጉባኤው ይመክራል። ለምግብ ስርዓት ሽግግር ስራዎች በአነስተኛ ወለድ የፋይናንስ አቅርቦትን ተደራሽ ማድረግ፣ አማራጭ የፋይናንስ ምንጮችን መጠቀም እና ሀገር በቀል የፋይናንስ መሰብሰብ አቅምን ማጎልበት ላይ ምክክሮች ይደረጋሉ ። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ በሮም በነበረው ጉባኤው ላይ ይፋ ያደረጓቸው ስድስት የትኩረት መስኮች አፈጻጸም ግምገማ ሌላኛው አጀንዳ ነው። በአፍሪካ መዲናዋ አዲስ አበባ የሚካሄደው ሁለተኛው የተመድ የስርዓተ ምግብ ጉባኤ የሀገራት መሪዎች እና ተወካዮች፣ ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ አርሶ አደሮች፣ አምራቾች እና የምግብ ስርዓት ሽግግር ተዋንያንን በአንድ መድረክ የሚያገናኝ ነው። በጉባኤው ላይ ከዋናው ሁነት ጎን ለጎን የምግብ ስርዓት ትራስፎርሜሽን እና የስርዓተ ምግብ ሽግግርን አስመልክቶ በርካታ የጎንዮሽ ስብስባዎች ይደረጋሉ። ኢትዮጵያ በምግብ ስርዓት ሽግግር ያከናወናቸውን ስራዎች አስመልክቶም በጉባኤው ተሳታፊዎች የመስክ ምልከታ ይደረጋል። ኢትዮጵያ በስርዓት ምግብ ትራንስፎርሜሽን፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ እና በግብርናው ዘርፍ ባደረጋቻቸው ሀገር በቀል ሪፎርሞች ያስመዘገበቻቸው ውጤቶች ጉባኤውን እንድታስተናግድ የተመረጥችባቸው ምክንያቶች ናቸው። ኢትዮጵያ በስርዓተ ምግብ ሽግግር እየተወጣች ያለው የመሪነት ሚና እና በማደግ ላይ ከሚገኙ ሀገራት በስርዓተ ምግብ ተምሳሌት የሆነች ሀገር መሆኗ ተመድ ዓለም አቀፉን ከፍተኛ ጉባኤ በኢትዮጵያ እንዲያደርግ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል። በጉባኤው ላይ ኢትዮጵያ የስርዓተ ምግብ ሽግግርን ለማሳካት እያከናወነች ባለው ተግባር ዙሪያ ተሞክሮዋን ለዓለም ማህበረሰብ የማስገንዘብ ስራ ታከናውናለች። ተባባሪ አዘጋጇ ጣልያን እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ በምግብ ስርዓት ሽግግር ውጤታማ ተሞክሮ ያላት ሀገር ናት። የደቡብ አውሮፓዊቷ ሀገር ከኢትዮዮጵያ ጋር በመሆን ጉባኤው የተሳካ እንዲሆን እየሰራችም ትገኛለች። ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የተመድ የስርዓተ ምግብ ጉባኤ ተሳታፊዎች ለማስተናገድ ዝግጅቷን አጠናቃ እየጠበቀች ትገኛለች።
በቻይና ይህም አለ!
Jul 8, 2025 675
በአብነት ታደሰ በርግጥ ከዓለማችን የጥንት ስልጣኔ ምድሮች አንዷ ናት- ቻይና። በታሪክ ገጾች ‘የግኝት ምድር’(Land of Invention) የሚል ተቀፅላ የሰፈረላት የሺህ ዘመናት ባለታሪክ ሀገር። የጥንት ቻይኖች አያሌ ‘ግኝቶችን’ ለዓለም አካፍለዋል። ወረቀት ፈብርከው ዘመናቸውን ጽፈዋል፣ ማተሚያ ቁስ ፈጥረው አትመዋል፤ ኮምፓስ ፈልስመው አቅጣጫ ጠቁመዋል።በ221 ዓመተ-ዓለም አንድ ወጥ ስርወ መንግስት መስርተው በሀገረ መንግስት የታሪክ ዑደት ከፍታንም ዝቅታንም አይተዋል። በቻይና አያሌ ስርወ መንግስታት ተፈራርቀዋል። ቻይናውያን ክፉውንም ደጉንም ችለው አልፋዋል። የሕዝቡ ጽናት፣ ጥበብ፣ ቱባ ባህል፣ ታሪክና ብልሃት በቻይና ግንብ ይመሰላል። ግንቡም ዝም ብሎ የጡብ ክምር አይደለም፤ የመሰረተ-ጽኑነታቸው ትዕምርት(symbol) እንጂ። ሲሶውን ሕዝቧ በያንግትዝ ወንዝ ተፋሰስ ጉያ አቅፋ፣ ጥንተ ማንነቷን ሸክፋ ዕልፍ ዘመናትን ተሻግራለች። የቻይና ስርወ መንግስታት ከስመው የዛሬዋ ኮሚኒስት ሪፐብሊክ ቻይና ከተመሰረተች ገና አንድ ምዕተ ዓመቷ ነው። ቅድመ ልደተ ክርስቶት በ221 ዓመተ-ዓለም የተመሰረተው ወጥ-ስርዎ መንግስት በመልከ ብዙ ምክንያቶች ተዳከመ። በፈረንጆቹ 1912 የመጨረሻው የቻይና ስርዎ መንግስት ተንኮታኮተ። ዘመናዊቷ የቻይና ሪፐብሊክ በዚህ ዘመን ተመሰረተች። ዳሩ ለውጡ አልጋ በአልጋ አልሆነም። ለሺህ ዘመን የጽኑ ስርዓተ መንግስት ባለቤቷ ሀገር ቻይና በአስከፊ የእርስ በርስ ጦርነት ታመሰች። ወረራንም፣ ዕልቂትንም አስተናገደች። በዘመኑ ማኦ ዘዶንግ የሚባል ባለራዕይ መሪ በቻይና ምድር ተነሳ። አርቆ አሰበ፤ ሀሳቡንም አሰረጸ፤ በዓላማ ጸንቶ ክፉ ዘመን ተሻገረ። ማኦ እና ተከታዮቹ ለቻይና ትንሳኤ ታተሩ። በጽናት ታገሉ። ለመስዕዋትነት ቆርጠው ተነሱ፤ ዋጋም ከፈሉ። በአውሮፓዊኑ ዘመን አቆጣጣር በ1949 የዛሬዋን የቻይና ሕዝባዊ ኮሚኒስት ሪፐብሊክ መሰረተ። ሃሳቡን ወደ ፖሊሲ ቀየረ፤ ተገበረውም። ቻይናን በኢንዱስትሪና ግብርና ምርት በንቅናቄ የማስፈንጠር ፕሮግራምንም (Great Leap Forward) ገቢራዊ አደረገ። ሆኖም ፖሊሲው በአንዴ ፍሬ አላፈራም። በወቅቱ በተፈጥሯዊና በሌሎች ምክንያቶች ቻይና በረሀብ ጠኔ ተመታች። ቻይናዊያን ተራቡ፤ ጎረቤት ሀገራትን ደጅ ጠኑ፤ ታላቁን ረሀብ መሻገር ያልቻሉ በአስር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ቻይናዊያን በረሀብ አለቁ። በቻንግሻ የሚገኘው የማኦ ዘዶንግ ግዙፍ ሐውልት መራራ ጽዋን ተጎነጩ። የሀገሪቷ መሪ ማኦ ዘዶንግ በወቅቱ ፈተና ተስፋ ሳይቆርጥ ሀገር አሻጋሪ ፖሊሲውን ገቢራዊ አደረገ። ልመናን ለትውልድ ላለማውረስ፣ ንቅዘትን(ሙስናን) ነውር የሚያደርግ ስርዓት አጸና። ስራን ወንጌል፤ ሙስናን ወንጀል ያደረገ ጽኑ ስርዓተ መንግስት ገነባ። ከራሷ አልፋ ለዓለም የተረፈችዋን የዛሬዋን ቻይና በጽኑ መሰረት ላይ አነበረ። የዛሬዋ ቻይና ከዓለማችን ቁንጮ ልዕለ ሃያል ሀገራት አንዷ ናት። ከራሷ አልፋ ለዓለም ተርፋለች፤ የቻይና ቴክኖሎጂ ምጥቀትና ርቀት ዓለም ጉድ አሰኝቷል። በቅርቡ ሀገረ ቻይናን ከጎበኙ ጋዜጠኞች አንዷ ሆኜ ‘መልክዓ ቻይና’ን በወፍ በረር ቃኘሁ። በዚህ ማስታወሻዬ በቻይና የቴክኖሎጂ ልህቀትና ምጥቀት ላይ ብቻ አተኩራለሁ። ከ1 ነጥብ 4 ቢሊዮን በላይ ህዝብ ባላት፣ በ14 ሀገራት በምትዋሰነው፣ በአንድ ኮሚኒስት ፓርቲ በምትመራው ሀገር ቻይና በነበረኝ የ15 ቀናት ቆይታ ቻይና እንደ ጥንተ ታሪኳ ሁሉ በዘመኑ የቴክኖሎጂና ፈጠራ ላይ ያላትን የመራቀቅ ጥግ ታዘብኩ። ዛሬን ብቻ ሳይሆን ነገን የመቅደም እሽቅድድሟ ‘አጃይብ’ ያሰኛል። በሀገሪቷ ርዕሰ መዲና ቤጂንግ እና በማዕከላዊ ቻይዋ በምትገኘው የሁናን ግዛት ዋና ከተማ ቻንግሻ ምልከታዬ ቻይና ’ከተባለላት በላይ’ የቴክኖሎጂ ምጥቀቷ አስደንቆኛል። ምናልባትም የመጀመሪያ ጉዞዬ መሆኑም ነገሩን በአንክሮት እንድመለከት ሳያስገድደኝ አልቀረም። የሀገሪቷ ርዕሰ መዲና ቤጂንግ እና ጥንታዊቷ ቻንግሻ ከ22 ሚለዮን የሚልቅ ህዝብ በጉያዋ የታቀፈችው ታላቋ ቤጂንግ ከተማ ከዓለማችን ግንባር ቀደም የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የባህል፣ የቱሪዝምና የዲፕሎማሲ ማዕከላት አንዷ ናት። የአዲስ አበባ እህት ከተማ በዚህ ወቅት ሞቃታማ አየር ጸባት አላት። ቤጂንግ የ21ኛው ክፍል ዘመን የኪነ ህንፃና ክትመት ቴክኖሎጂ ያበበች ብቻ አይደለችም፤ ይልቁኑም በዛፎች ሀመልማላዊ ገጽታ የተላበሰች ውብ መዲና እንጂ። በሕንፃዎችም፣ በዛፎችም የተደነነች ከተማ። በተፈጥሮ የበቀሉ የሚመስሉ ሰማይ ታካኪ ሕንጻዎች፤ የመንገድ መሰረተ ልማት ስፋት፣ ጽዳትና ጥራት ‘ኩልል’ ያለች፣ ‘ምልል’ የምታደርግ ከተማ ያደርጋታል። ቤጂንግ ከተማ ከዘመናችን አስደናቂ የቴክኖሎጂ ውጤቶች አንዱ በሆነው የሰው ሰራሽ አስተውሎት(አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ) ሕይወትና ኑሮን እንዴት እንዳቃለለ የቤጂንግ የዕለት ከዕለት ክዋኔ ሁነኛ ማሳያ ነው። ቻይኖች በሰው ሰራሽ አስተውሎት ተጠበዋል፤ መጠበብ ብቻም ሳይሆን ኑባሬያቸውን ሰው ሰራሽ አስተውሎት መር አድርገዋል። ከሮቦት መስተንግዶ እስከ ሰው ሰራሽ ፀሐይ መራቀቅ ይስተዋላል። ካረፍኩበት ሆቴል (15ኛ ወለል ላይ ከሚገኘው መኝታ ክፍሌ) ሆኜ ያዘዝኩት ምግብ በቅጽበት አስተናጋጇ ‘ከች’ ብላ ትደውላለች። ፍጥነቷ ስትገረም፤ አስተናጋጆች ሮቦቶች መሆናቸውን ስትመለከት ይበልጥ ትደነቃለለህ። በክፍሌ ውስጥ ማብሪያ ማጥፊያ ስጫን መጋረጃው ሲከፈት መደንገጤን አልሸሽግም፣ ከምሽቱ 3 ሰዓት ፀሐይ አለመጥለቋን ስመለከት ‘የቻይና ሰው ሰራሽ ፀሐይ ወጣች እንዴ?’ ማለቴ አልቀረም። በነገራችን ላይ የቻይና የሰው ሰራሽ ፀሐይ ሳይንሳዊ ፈጠራ ሁለት ግዜ ተሞክሮ ያለምንም እንከን እንደሚሰራ ነግረውናል። የሰው ሰራሽ ፀሐዩ ሃይድሮጅን እና ዱተሪየም ጋዞችን እንደ ሀይል ማመንጫ ነዳጅነት በመጠቀም ንጹህ ኢነርጂን ለማመንጨት ታስቦ ዲዛይን እንደተደረገና ሰው ሰራሽ ፀሐይ በርሐን ከተፈጥሮ ፀሐይ 13 እጥፍ ያክል ሙቀት እንደሚያመነጭም ሰምተን ተደንቀናል። የቻይና ሰው ሰራሽ ፀሐይ ፕሮጀክት የሥራ ሰዓትን ከ13 ሰዓት ወደ 24 ሰዓት ለመጨመርና ምርታማነትን ለማሳደግ ግብ የሰነቀ ነው። በቻይና በሰዉ ቅርፅ የተሰሩ ሮቦቶች በእግር ኳስ ጨዋታዎች ተወዳጅነት አትርፈዋል። ቤጂንግ የሚገኘው ሂዩማኖይድ የተሰኘ የሮቦት ቡድን የሰራቸው ሮቦቶች አመርቂ ውጤት ከራቀው የሀገሪቷ እግር ኳስ ቡድን ይልቅ የሀገሬውን ቀልብ እንደሳቡ ይነገራል። በሰው ሰራሽ አስተውሎት በታገዘ የሮቦቶች ውድድር አያሌ ቻይናዊያን ይታደማሉ። ሮቦቶቹ በጨዋታ መሐል ቢወድቁ በራሳቸውን ይነሳሉ፤ ቢጎዱም ከሜዳ የሚወጡበት ስርዓት ተዘርግቷል። የታላቋ ቻይና ሰዎች ቴክኖሎጂን ከችግር መፍቻነት ወደ መዝናኛነትም አልቀውታል። በሀገራችን እንደ አዲስ ቴክኖሎጂ በንግዱ ስርዓት ውስጥ እየተዋወቀ ያለው የፈጣን ምላሽ መለያ ወይም ኪው አር ኮድ(Quick Response code) በቻይና ዕለታዊ ከዋኔዎች ቅንጦት አይደለም። በቻይና ማንኛውም ግልጋሎት በዚህ በዲጂታል ስርዓት ይከወናል። እንደሌሎች ስልጡን ሀገራት ሁሉ በንክኪ የሚደረግ ገንዘብ ዝውውር ቀርቷል። በቤጂንግ ጎዳናዎች በኪው አር ኮድ(QR Code) በሚንቀሳቀሱ ሞተር ሳይክሎችን በየመንገዱ ተሰድረዋል፤ የፈለገ መንገደኛ ሳይክሎችን በመጠቀም ወደ ፈለገበት ስፍራ ተንቀሳቅሶ ክፍያውን በኪው አር ኮድ ከፍሎ ይሄዳል። ሌላውም እንዲሁ። በአዲስ አበባ መኖሪያ ሰፈሬ የነበሩ ሳይክሎኝ ከደጃችን ደብዛቸው እንደጠፋ ሳስብ በቻይኖች ብልሃት፣ ታማኝነትና የከተሜነት ልህቀት ቀናሁ። በርግጥ በቻይና ኪው አር(QR) ኮድ ለተገለገልንበት መክፈያ ብቻ ሳይሆን ለልመናም መዋሉን ሲመለከቱ ፈገግ ሊሉ ይችላሉ። በቻይና ይህም አለ በማለት። በርግጥ በቤጂንግ የሰው እጅ ከሚያይ ይልቅ ጆሮቸውን ቢቆጥርጣቸው የሚሰሙ የማይመስሉ አዛውንቶች ሳይቀር በስራ ላይ ተጠምደው ይስተዋላሉ። ከቻይናውያን ጋር ለመግባባት በተለይም በንግድ ማዕከላት የቻይንኛ ቋንቋ መረዳት ግድ ይላል። “ሃው ማቺ፣ ጉዳ ጉዳ፤ ሺሼ፣ ኢ፣ አር…” እና መሰል ቃላት ማወቅ ይበጃል። ከዚህ ባለፈ በምልክት መግባባት አልያም በቋንቋ ተርጓሚ መተግበሪያ መጠቀም ያሻል። የቻይና ሰራሽ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ምርቶች በራሳቸው ብራንድ፣ ቋንቋና መልክ እየተመረቱ በተመጣጣሽ ዋጋ ለህዝቦቿ ተደራሽ እየተደረጉ ነው። የቻይና የራስ-በቅነት ጥረት ያስቀናል። በቴክኖሎጂ፣ በባሕልና በኢኮኖሚ ተጽዕኖ ተላቀው በራሳቸው ለመቆም የሄዱበት ርቀት ግሩም ነው። ግብይቶች በራሳቸው ገንዘብ ብቻ ይከወናል። በወቅቱ ምንዛሬ አንድ የአሜሪካ ዶላር ሰባት የቻይና ገንዘብ(ዩዋን) ነው። ከምዕራባዊያን ማህበራዊ ትስስር ገጾች(ለምሳሌ ፌስቡክ፣ ቴሌግራም፣ ዩቲዩብ፣ ቲክቶክ) በሕግ በማገድ የራሳቸውን መተግበሪያ አበልጽገው ገቢራዊ አድርገዋል። ‘ዊቻት’ የተሰኘው መተግበሪያ ሁሉም ቻይናውያን መገልገያ ነው። ከቤጂንግ ሌላ ያስደነቀችኝ ጥንታዊቷ ቻንግሻ ከተማ ነች። ቻንግሻ ስመ-ብዙ ነች። ከሶስት ሺህ ዓመታት በላይ ዕድሜ ጠገቧ የሁናን ግዛት ርዕሰ መዲና ቻንግሻ ‘የከዋክብት ከተማ’ ትሰኛለች። በነገራችን ላይ ማኦ ዘዶንግ ትውልዱ ሁናን ግዛት ውስጥ ነው። ቻንግሻ በስራ ከተማነቷ ‘የማታንቀላፋው መዲና’ ትባላለች። በመዝናኛ ስፍራነቷ ‘የተዝናኖት መነሃሪያ’ የሚል ተቀጥላ ስም አላት። ‘የሚዲያ ጥበብ’ ስፍራም ትሰኛለች። በኢንዱስትሪ፣ በጥንታዊ ሐውልቶች፣ አብያተ መቅደሶች፣ ታሪካዊ ስፍራዎች መገኛ በመሆኗ በቱሪስቶች ተወዳጅ ከተማ ናት። ትናንትና ዛሬን ያዋደደች፣ ታሪክና ባህል ባዛነቀችዋ ቻንግሻ የአምስት ቀናት ቆይታዬ ብዙ ገጽታዋ አስደምሞኛል። የሻንግ ወንዝን ተንተርሳ፣ በተራራማ፣ በሜዳማና ኮረብታማ መልክዓ ምድር በማዛነቅ የተቆረቆረች በመሆኗ የስብት ማዕከል ሆናለች። እንደ ቤጂንግ በደን የተከበበች፣ በዘመነኛ ሰማይ ጠቀስ ሕንፃዎች እና በታሪካዊ ኪነ ሕንጻዎች የተጌጠች ከተማ ናት። ከዚህ ባሻገር የአምራች ኢንዱስትሪዎች መናገሻም ናት። የምቹ ከተሜነትና ጠንካራ የስራ ባህል በግላጭ የሚስተዋልባት ከተማ። የዓለማችን ገዙፉ በጣም ሞቃታማ አየር ጸባይ ባላት ቻንግሻ ሌት ከቀን ይሰራል። ፋብሪካዎቿ አይተኙም። ሌትና ቀኑ የሚታወቀው በሰዓት ብቻ እንጂ የስራና የንግድ ድባቡ እኩል ነው። ብርሃናማዋ ቻንግሻ ‘የቻይዊያን መስቀል’ በተሰኘው በቀይ በተቀለመው መስቀልም ትታወቃለች። በርግጥ ከዓለማችን ግዙፍ ማማዎች አንዱ የሆነው ሕንጻም መገኛ ናች። በጥቅሉ የቻይና ጉብኝት ትዝብቴ የገናና ታሪክ ባለቤቷ ሀገር ከባድ ውጣ ውረዶችን አልፋ ዛሬ ዓለምን እየቀደመች መሆኑን ሳስብ፤ እንደቻይና ሁሉ የሺ ዘመናት ገናና ታሪክና አኩሪ ገድል ያላት ኢትዮጵያስ የሚል ተጠየቅ እንዳውጠነጥን አድርጎኛል። ቻይናዊያን የዘመን የፈተና ቋጠሮዎቻቸውን ፈታተው ከዛሬ ከፍታ ሰገነት ላይ ወጥተዋል። ከዛሬም በበለጠ ነገን በጽኑ መሰረት ላይ እየገነቡ ነው። እኛስ? ብዬ ሳስብ በቁጭትና በተስፋ ተዋጥኩ! ሰላም!
በ17ኛው የብሪክስ ጉባኤ ላይ መሪዎቹ ምን አሉ?
Jul 7, 2025 391
በ17ኛው የብሪክስ ጉባኤ ላይ መሪዎቹ ምን አሉ? 17ኛው የብሪክስ የመሪዎች ጉባኤ በብራዚል ሪዮ ዴጄኔሮ እየተካሄደ ይገኛል ጉባኤው እየተካሄደ የሚገኘው “ ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ የደቡብ ንፍቀ ዓለም” በሚል መሪ ሀሳብ ነው። በጉባኤው ላይ ተሳታፊ የሆኑ የብሪክስ አባል እና አጋር ሀገራት መሪዎች እና የዓለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮች በዓለም አንገብጋቢ እና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ሀሳባቸውን ሰንዝረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ብሪክስ ከጠንካራ አዲስ ሀሳብ ተነስቶ ለዓለም አቀፍ ለውጥ የሚሰራ ብርቱ ኃይል ወደመሆን ተሸጋግሯል። ዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማት የጋራ ደኅንነትን እና ሁሉን አካታች ብልጽግናን ለማምጣት በሚያስችል ሁኔታ አፋጣኝ ማሻሻያ ማድረግ አለባቸው። በብሪክስ አዳዲስ አባላት መጨመራቸው የጋራ ድምፃችን የበለጠ ይጠናከራል። የጋራ አላማችን የበለጠ ይጠራል። አቅማችንም ይሰፋል። እንደ ብሪክስ አባልነቷ ኢትዮጵያ እነዚህ ጥረቶች እንዲሳኩ በተለይም በአለምአቀፍ ውሳኔ ሰጪ መድረኮች ለአዳዲስ ገበያዎች እና በማደግ ላይ ላሉ ሀገራት ሰፋ ያለ ውክልና በሚገኝበት ሁኔታ ላይ በንቃት አስተዋፅኦ ታደርጋለች። የብራዚል ፕሬዝዳንት ሉዊስ ኢግናሲዮ ሉላ ዳ ሲልቫ የዓለምን የአስተዳደር ስርዓትን ለመቀየር የሚያስችል መሰረተ ልማትና የጋራ ትብብራችንን ማጠናከር ይገባል። ብሪክስ ለ21ኛው ክፍለ ዘመን የሚሆን አዲስ የብዝሃ ዓለም አስተዳደር የመፍጠር ቁልፍ ሚና አለው። ከጦርነት ይልቅ ሰላም ላይ መዋዕለ ንዋይን ማፍሰስ ትርፋማ ያደርጋል። የበለጸጉ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ቃል የገቡትን ገንዘብ መስጠት አለባቸው። የቻይና ጠቅላይ ሚኒስትር ሊ ኪያንግ ብሪክስ በዓለም ፍትሃዊ እና መርህን ያከበረ የዓለም ስርዓት እንዲፈጠር የመሪነት ሚናውን መወጣት አለበት። ለብሪክስ ሀገራት የኢኮኖሚ እድገት ልማት ትልቅ ድርሻ ያለው የእድገት ምሰሶ ነው። በብሪክስ ሀገራት መካከል ያለውን የባህል ልውውጥ እና የጋራ መማማር የበለጠ ማሳደግ ይገባል። ብሪክስ በዓለም ደረጃ ያሉ ግጭቶች በውይይት እና በንግግር እንዲፈቱ በማድረግ የሰላም ኃይል መሆኑን በተጨባጭ ማሳየት ይኖርበታል። የሩሲያ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን (በበይነ መረብ) ሊበራሊዝም መር የሆነው የዓለም የሉላዊነት አስተዳደር ስርዓት ጊዜው አልፎበታል፤ አዲስ የባለብዝሃ የዓለም ስርዓት እያቆጠቆጠ ነው። በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በራሳቸው ገንዘብ የመገበያያት ልምምዳቸውን ማጠናከር አለባቸው። የብሪክስ ሀገራት በተፈጥሮ ሀብት፣ ሎጅስቲክስ፣ ንግድ፣ ፋይናንስ እና በሌሎች መስኮች ያላቸውን ትብብር ማጠናከር አለባቸው። በሚሸፍነው መልክዐ ምድር፣ በያዘው የህዝብ ብዛት እና በዓለም ኢኮኖሚ ውስጥ ባለው ድርሻ ብሪክስ ትልቅ ኃይል ሆኗል። የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ዓለም አቀፍ ተቋማት የደቡብ ንፍቀ ዓለምን ፍትሃዊ ውክልና በሚያረጋገጥ መልኩ ሁሉን አቀፍ ሪፎርም ሊደረግበት ይገባል። የ21 ክፍለ ዘመን ሶፍትዌር በ20ኛ ክፍለ ዘመን የታይፕ ራይተር ማሽን ላይ ግልጋሎት ሊሰጥ አይችልም። የሰው ልጅ እና የዓለማችን የምንግዜውም ትልቅ ስጋት ሽብርተኝነት ነው። ሽብርተኝነት መከላከል እና ማውገዝ የሁሉም የጋራ ኃላፊነት ነው። የሰው ሰራሽ አስተውሎት ኃላፊነት በተሞላበት መልኩ መጠቀም እና ማስተዳደር በጣም አስፈላጊ ነው። ህንድ በዓለም ደረጃ ያሉ አለመግባባቶች በዲፕሎማሲ፣ በሰላም እና በንግግር እንዲፈቱ በቁርጠኝነት ትሰራለች። የደቡብ አፍሪካ ፕሬዝዳንት ስሪል ራማፎሳ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ወቅታዊ የዓለም ነባራዊ ሁኔታን መሰረት ያደረገ አፋጣኝ ማሻሻያ ያስፈልገዋል። ብሪክስ ዓለም አቀፍ የጂኦ ፖለቲካ ውጥረቶችን ለመፍታት፣ ዘላቂ ሰላም ለማስፈን እና አሳታፊ የደህንነት ማዕቀፎችን ማረጋገጥ የሚያስችል የጋራ አሰራር መፍጠር አለባቸው። ደቡብ አፍሪካ የብሪክስ የፀረ-ሽብርተኝነት ስትራቴጂ ውጤታማ በሆነ ሁኔታ ለመተግበር ቁርጠኛ ናት። የብሪክስ መስፋት ንግድ ፣ ቴክኖሎጂ ሽግግር እና አረንጓዴ ኢኮኖሚን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች አዳዲስ የትብብር አማራጮችን ይፈጥራል። የኢንዶኔዥያ ፕሬዝዳንት ብራቦዎ ሱቢያንቶ ብሪክስ በደቡብ-ለደቡብ ሰላም፣ ደህንነት፣ ሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ የዓለም ጤና እና የከባቢ አየር ትብብር ወሳኝ ሚና እየተጫወተ ነው፡፡ የዓለም የብዝሃ ወገን ተቋማት እኩልነትን ይበልጥ የሚያረጋግጥ ለውጥ ያስፈልጋቸዋል። በኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ አማካኝነት በብሪክስ እና በምዕራቡ ዓለም መካከል ሚዛናዊ ትብብር መፍጠር ይገባል። በዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ ኢ-ፍትሃዊ አካሄድ እና ጦርነት እንደ አማራጭ መጠቀም ሊቆም ይገባል። ዓለም አቀፍ ፍትህ እና ሰላምን ማስፈን ጊዜ ሊሰጠው የማይገባ ጉዳይ ነው። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ዓለም ከምንጊዜውም በላይ ሰላም ያስፈልጋታል። ግጭቶችን በውይይት እና በንግግር መፍታት አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው። የሰውን ህይወት እና ኢኮኖሚ በፍጥነት እየቀየረ ያለውን የሰው ሰራሽ አስተውሎትን ለእኩይ አላማ እንዳይውል በከፍተኛ ኃላፊነት እና ጥንቃቄ መጠቀም ይገባል። ብዝሃ ዓለም የባለብዝሃ ወገን አስተዳር ስርዓት ያስፈልገዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት እና የዓለም የፋይናንስ መዋቅርን ጨምሮ የዓለም የአስተዳደር ስርዓት ከጊዜው ጋር ተራማጅ መሆን አለበት። በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በዓለም ኢኮኖሚ እና አስተዳደር ውስጥ ያላቸውን ተሳትፎ የበለጠ ማሳደግ ይገባል። ሁለተኛ ቀኑን የያዘው 17ኛው የብሪክስ የመሪዎች ጉባኤ ዛሬ የተለያዩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።