መጣጥፍ - ኢዜአ አማርኛ
መጣጥፍ
“ዮ-ማስቃላ''- ሁሉም የሚደሰትበት በዓል
Sep 23, 2023 792
በሳሙኤል አየነው የሰላም፣ የአብሮነት፣ የፍቅር፣ የመቻቻልና የአንድነት ተምሳሌት የሆነው የጋሞ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል “ዮ-ማስቃላ” ከወርሃ መስከረም አጋማሽ ጀምሮ በተለያዩ ባህላዊ ሁነቶች በድምቀት ይከበራል ። በተለያየ ምክንያት በሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ ተራርቀው የነበሩ ወገኖች ወደ የአካባቢያቸው በመመለስ ከቤተሰቦቻቸው ብሎም ከቀየው ህብረተሰብ ጋር አብረው የሚያከብሩት የዓመቱ ታላቅ በዓል ነው ። ታዲያ በዓሉን በድምቀት ለማክበር ወንዶች ሰንጋ በሬ ለመግዛት እንዲሁም ለትዳር አጋሮቻቸውና ለልጆቻቸው ልብስና ጌጣ ጌጥ የሚሆን ገንዘብ መቆጠብ የሚጠበቅባቸው ሲሆን ሴቶችም ለባህላዊ ምግቦች፣ ለቅመማ ቅመም፣ ለቅቤና ለባህላዊ መጠጦች እህል ግዥ የሚሆን ገንዘብ ዓመቱን ሙሉ ሲቆጥቡ ይከርማሉ። መስከረም ወር ከገባበት ዕለት አንስተው ወንዶችም ሆኑ ሴቶቹ በቆጠቡት ገንዘብ በየፊናቸው ለበዓሉ የሚሆኑ ቁሳቁሶችን ማቅረብ ይጀምራሉ። ይህም የዝግጅት ጊዜ “እንግጫ” በመባል ይጥራል። በ”ዮ--ማስቃላ” ጊዜ አብሮነት እንጂ ግለኝነት የሚባል ነገር በጋሞዎች ዘንድ ፈጽሞ አይታሰብም፤ አብሮ እርድ ማካሄድ፣ አብሮ መመገብ፣ አብሮ መጠጣት፣ አብሮ መጫወት የጋሞዎች መገለጫ ነው። እንደ ሌሎቹ በዓላት ሁሉ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖችም በዓሉን እንዴት እናሳልፍ የሚል ስጋት አያድርባቸውም። ምክንያቱም የሌለውም ካለው ጋር አብሮ የሚቋደስበት፣ የሚደሰትበት፣ የሚተሳሰብበትና የሰብአዊነት ልክ የሚንጸባረቅበት ልዩ ድባብ ያለው በዓል ነውና ዮ-ማስቃላ ። የጋሞ የሀገር ሽማግሌ አቶ አመሌ አልቶ ስለ “ዮ--ማስቃላ” በዓል በትንሹ እንዲያወጉን ጠይቀናቸው በዓሉ ለሰው ልጆች ብቻ ሳይሆን እንስሳትና አዕዋፋት ሁሉ የሚደሰቱበት እንደሆነ ነግረውናል። በአካባቢው ቋንቋ ተፈጥሮ ሁሉ በዓሉን በደስታ እንደሚያሳልፍ ለመግለጽ “ካፎስ ካናስ ማስቃላ” በማለት የሚገለጽ ስሆን “ለሰው ብቻ ሳይሆን ለእንስሳትም መስቀል ነው” እንደማለት ነው ብለዋል። በዓሉ ከመድረሱ ከሶስት ወራት አስቀድሞ በየአካባቢው ለእንስሳት የግጦሽ ሥፍራ ተከልሎ የሚዘጋጅ ሲሆን ችቦው በሚለኮስበት በደመራው ዕለት የቤት እንስሳት በሙሉ በዚያው የሚሰማሩ ይሆናል። ዓመቱን ሙሉ ሲያርሱ የነበሩ የእርሻ መሣሪያዎችም በበዓሉ ጊዜ ታጥበውና በቅቤ ታሽተው በክብር ይቀመጣሉ። ክብር ለሰው ልጆች ብቻ ሳይሆን ለእንስሳትና ለእርሻ መሣሪያዎችም ይሰጣል። በባህሉ መሠረት ችቦ በሚወጣበት ሰዓት አባት የራሱን ችቦ ለኩሶ የቤቱን ምሰሶ፣ የከብቶችን ጋጣና የበር ጉበኖችን ግራና ቀኝ በችቦው ጫፍ በማነካካት ወደ ውጭ ካወጣ በኋላ ወንድ ልጆች የየራሳቸውን ችቦ ተራ በተራ እየለኮሱ አባታቸውን ተከትለው “ዮ---ማስቃላ” እያሉ ወደ ደመራ ቦታ ያመራሉ። ከዚያም አባት በቅድሚያ ችቦውን ከለኮሰ በኋላ ልጆች ደግሞ ተከትለው ደመራውን ይለኩሳሉ። ከዚህ ፕሮግራም መልስ ወደ ቤት ተመልሰው የተዘጋጀውን ገንፎ በአንድ ወጭት ላይ “ዮ--ማስቃላ”እያሉ ሁሉም የቤተሰብ አባላት፣ ዘመድ አዝማድና ጎረቤት ተሰባስበው በጋራ ይመገባሉ። በ”ዮ--ማስቃላ” በዓል በዋናነት እርድ የሚከወን ሲሆን ቁርጥ፣ ጎረድ ጎረድ፣ ክትፎና የወጣ ወጥ ዓይነቶች ተሠርተው ለምግብነት ይቀርባሉ። ከባህላዊ ምግቦች ደግሞ የገብስ ቅንጬ፣ የቆጮና ገብስ ውህድ ቂጣ፣ የቡላ ፍርፍር፣ ሀረግ ቦዬ፣ እንዲሁም ከመጠጥ አይነቶች ደግሞ ቦርዴ፣ ጠላ፣ የማርና የቦርዴ ጠላ ውህድና ሌሎች ተወዳጅ ምግቦችና መጠጦች ይዘጋጃሉ። በ”ዮ--ማስቃላ” በዓል ዕለት የሚቀራረቡ ጎረቤታሞች በጋራ ሆነው አማካይ በሆነ ሥፍራ ላይ የእርድ ሥነሥርዓት ያከናውናሉ። የእርድ ሥነ-ሥርአቱም በደመራው ዕለትና ማግስት እንደ ህብረተሰቡ ይሁንታ የሚፈጸም ይሆናል። ከማግስቱ ጀምሮ የተዘጋጀውን ሥጋ በጋራ እየበሉና እየጠጡ የበዓሉን ድባብ የሚያስቀጥሉ ሲሆን “ዱንግዛ” በተሰኘው የጋሞ ባህላዊ ጥበብ ልብስ ደምቀው በጌጣጌጥ አሸብርቀው ሁሉም በየአደባባዩ በባህላዊ ጫዋታዎች እየተደሰተ በዓሉን ያከብራል። ሰላም፣ ፍቅር፣ አንድነትና አብሮነት ካለ በአዲሱ ዓመት ምድሪቱ ተገቢውን ምርት እንደምትሰጥ ሁሉም ሰው በተሰማራበት መስክ ውጤታማ እንደሚሆን ይታመናል። ከዚም የተነሳ በአሮጌው ዓመት ሃዘን ላይ የነበሩ ወገኖች ሙሉ በሙሉ ሀዘናቸውን በመተው በአዲስ መንፈስ ወደ መደበኛው ህይወት ይመለሳሉ። የተጣሉ ወገኖች ቂም ይዘው አዲስ ዓመትን መሻገር በጋሞዎች ዘንድ ነውር በመሆኑ በባህላዊ ሸንጎ ሥርአት /ዱቡሻ/ በጋሞ አባቶች አሸማጋይነት እርስ በርስ ተነጋግረው በመታረቅ አዲሱን ዓመት በጋራ ያበስሩታል። በሌላ መንገድ “ዮ..ማስቃላ” በዓል ተጠብቆ ወጣቶች የሚተጫጩበት፣ የተጫጩት ደግሞ ጋብቻ የሚከውኑበት እንዲሁም ያገቡት በየገበያው ዕለት “ሶፌ” የሚባል ሥነ-ሥርዓት በማከናወን በማህበራዊ ህይወት ማህበረሰቡን በይፋ የሚቀላቀሉበት መሆኑን ጋሽ አመሌ አውግተውናል። ጋሞዎች ከሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች ጋር በመሆን በአብሮነት ለሁለት ሳምንታት በደስታ ካሳለፉ በኋላ ወደ ግብርና ሥራቸው በመመለስ ቀደም ሲል በክብር ያስቀመጧቸውን የእርሻ መሣሪያዎች በማንሳት ወደ እርሻ ሥራ ይገባሉ። እስከ ታህሳስ ወር መውጫ ድረስ የበዓሉ ድባብ ሳይጠፋ ይቆይና በመጨረሻም የመሰናበቻ ድግስ ወይም “ጮዬ ማስቃላ” በማዘጋጀት በህብረት ከተመገቡና ከጠጡ በኋላ የዓመት ሰው ይበለን፣ ዓመቱ የሰላም፣ የጤና፣ የበረከት ይሁን በማለት በመመራረቅ “ዮ--ማስቃላ”ን ይሸኛሉ። በዓሉ የህዝቡን ሰላም ፣አንድነትና አብሮነት የሚያንጸባርቅ ልዩ በዓል ነው በማለት የጋሞ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ አቶ ሞናዬ ሞሶሌ የጋሞ የሀገር ሽማግሌ የሆኑት የአቶ አመሌ አልቶን ሃሳብ ይጋራሉ። ባህላዊ እሴቱ ከትውልድ ወደ ትውልድ ተጠብቆ እንዲቆይ “ዮ--ማስቃላ” ትልቅ ድርሻ አለው። የባህል እሴቶች ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፉ በጥናትና ምርምር በማስገፍና የቋንቋና ባህል አውደ ጥናት በየዓመቱ እየተደረገ እንደሆነም ነግረውናል። አባቶች በልዩነት ውስጥ ያለንን አንድነት እንዳቆዩልን ሁሉ ወጣቶችም ኢትዮጵያዊ ለዛ ያላቸው የጋራ እሴቶች ሳይበረዙና ሳይከለሱ ጠብቀው ለትውልድ የማስተላለፍ ሃላፊነት አለባቸው የሚለውን የንግግራቸው ማሳረጊያ አድርገዋል።
የዕልፍ ሕጻናትን ዕጣ ፈንታ ከሞት ወደ ሕይወት የለወጠው ወጣት ላሌ ላቡኮ
Sep 8, 2023 1190
በሀገራችን በርካታ አካባቢዎች የታዳጊዎችን ተስፋና ህልም ብቻ ሳይሆን ሕልውና የሚገዳደሩ ከባህላዊ እምነት ጋር የተቆራኙ አይነተ ብዙ ጎጂ ባህላዊና ልማዳዊ ድርጊቶች እና ክዋኔዎች አሉ። ለአብነትም ደቡብ ኦሞ ዞን እንደ ካራ፣ ሀመርና ቤና ህዝቦች ዘንድ የተለመደው እና ከህጻናት ጥርስ አበቃቅል ጋር የተያያዘው ’ሚንጊ' የሚሰኘው ጎጂ ልማዳዊ ድርጊት ይጠቀሳል። በአካባቢው ልማድ በታችኛው ድድ ጥርስ የሚያበቅሉ እንስሳት ቅዱስ፣ በላይኛው ድድ ጥርስ የሚያበቅሉ እንስሳት ደግሞ ርኩስ የሚል ስያሜ ይሰጣቸዋል። ከዚህ ጋር በማገናኘትም የሚወለዱ ህጻናት የላይኛው የወተት ጥርሳቸው ቀድሞ የሚበቅል ከሆነ እንደ እርኩሳን እንስሳት ከመጥፎ መንፈስ ጋር ተቆጥሮ ለማህበረሰቡ የማይበጅ፣ አድጎም ለቤተሰቡ ጠንቅ ተቆጥሮ የመገደል ዕጣ ፈንታ ይገጥመዋል። ይህ ልማድ “ሚንጊ” ተብሎ የሚጠራ ሲሆን አያሌ ህጻናትን ቀጥፏል። ይህ ብቻም ሳይሆን የማህበረሰቡ አባል ሴት ከትዳር በፊት ልጅ ከወለደች የተወለደው ሕጻን በ'ሚንጊ'ነት ይፈረጃል። ሚንጊ ተብለው የተፈረጁ ህጻናት በማህበረሰቡ ዘንድ መርገምት፣ ቁጣ፣ ርሀብ በሽታ… እንደሚያመጡ ስለሚቆጠር ከጥልቅ ወንዝ መጣል፣ ወደ ገደል መወርወር አልያም በጫካ ውስጥ የመጣል ዕጣ ይገጥማቸዋል። ሚንጊንና መሰል በየማህበረሰቡ ዘንድ ለዘመናት የተለመዱ ጎጂ ድርጊቶችን ለማስቀረት እና ማህበረሰብ አቀፍ ለውጥ ለማምጣት ግን ውስብስብ እና ጊዜ የሚጠይቅ ጉዳይ ነው። ላሌ ላቡኮና መሰል ብርቱና አርቆ አሳቢ ሰዎች ግን ባደጉበት ብርቱ ጥረት የማህብረሰብን አስተሳስብ በመለወጥ ለዘመናት ለሚከወኑ ውስብስብ ችግሮችን መፍትኤ መስጠት ችለዋል። ላሌ ላቡኮ በተወለደበት ቀዬ እና አባል በሆነበት ደመ ከልብ ሆነው የሚቀሩ ህጻናትን ዕጣ ፈንታ ከወንዝ፣ ከገደልና ከጫካ ከመጣል ተርፈው ለወግና ማዕረግ እንዲበቁ አስችላል። በአጉል ባህል ሕይወታቸውን የሚነጠቁ ዕልፍ አዕላፍ ህጻናት ነፍስ እንዲዘሩ በማድረግ ትውልድ ያሻገረ፣ ማህበረሰብን የለወጠ አርበኛ ነው። ላሌ ላቡኮ ይህን ነባር ጎጂ ልማዳዊ ድርጊት ለመቃወምና መፍትሄ ለማምጣት ያነሳሳው ሁለት እህቶቹን ጨምሮ ምንም ነፍስ ያላወቁ ሕጻናት በሚንጊነት ተፈርጀው ሲቀጠፉ በማየቱና በመስማቱ እንደሆነ ይናገራል። ከ17 ዓመታት በፊት ‘ኦሞ ቻይልድ’ በሚል ባቋቋመው ድርጅት 'ሚንጊ' የተባሉ 58 ሕፃናትን ከገዳዮች ፈልቅቆ ከሕልፈት ወደ ሕይወት ለውጧል፣ ለቁም ነገር ለማብቃትም እያስተማራቸው ይገኛል። እህቶቹን ጨምሮ የትውልድ መንደሩ ሕጻናትን ሕይወት ለመቀጠፍ የዳረጋቸው የሚንጊ ድርጊት የሚፈጸመው፣ በማህበረሰቡ ዕውቀት ማነስ ነው ብሎ ያምናል። በዚህም ይህን አስከፊ ድርጊት እና አስተሳሰብ ለመቀየር ቆርጦ በመነሳቱ ቤተሰቡን ጨምሮ ከማህበረሰቡ መገለል እስከ ማስፈራሪያ ጥቃቶች አስተናግዷል። እርሱ ግን ፈተናዎች ሳይበግሩት በዓላማው ጸንቶ፣ ትዕግስትና ብልሃት ተላብሶ ሸውራራ ማህበረሰብ አቀፍ አመለካከቶችን መስበር ችሏል። የሚንጊ ባህል አሁንም ሙሉ ለሙሉ እንዳልተቀረፈ የሚናገረው ላሌ፣ ስር ነቀል የአስተሳስብ ለውጥ ለማምጣት ለህብረተሰቡ አሁንም ብርቱ ግንዛቤ የመፍጠር ስራዎች እንደሚገቡ ገልጿል። ላሌ በመሰረተው ድርጅት ከሚማሩ ሕጻናት ባሻገር ከ300 በላይ ህጻናት ከቤተሰባቸው ዘንድ ሆነው ለመማር እንዲችለኩ ማድረጉንም ይናገራል። ሕፃናቱን ከሞት አፋፍ ታድጎ ከራሳቸው ሕልውና ባለፈ ለቁም ነገር እንዲበቁና ለሀገርና ለወገን የሚበጁ ሰዎች እንዲሆኑ በመስራቱ አዕምራዊ እርካታ እንደሚሰማው ይገልጻል። ላሌ የሚንጊን ጎጂ ድርጊት ከመታደጉ በተጨማሪ በደቡብ ኦሞ ትምህርት ቤት ገንብቶ ከ700 በላይ ተማሪዎችን እያስተማረ ይገኛል። ናሽናል ጂኦግራፊ፣ ቴድ ቶክ፣ የሰብዓዊ መብቶች ተቋም እና የበጎ ሰው ሽልማት ድርጅት የላሌን ትውልድ የመታደግ ተግባር ዕውቅና ከሰጡት ወስጥ ይጠቀሳሉ።
የ19ኛ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዎና ደጋሹ የቡዳፔስት ስታዲየም
Aug 22, 2023 1124
የቡዳፔስቱ ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየም 700 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በሚጠጋ ገንዘብ ተገንብቶ ዝግጅቱን አሟልቶ እንዲያስተናግድ በሚያስችል ቁመና ላይ የደረሰው ከ19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዎና መጀመር ቀደም ብሎ ነው። የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከኦሊምፒክ ጨዋታዎች ቀጥሎ የሚጠቀስ ግዙፍ የሆነ ዓለም አቀፍ የስፖርት ሁነት ነው። “የስፖርቶች ንጉስ” የሆነ ውድድር ነው የሚሉትም አልጠፉም። አገራት ለሻምፒዮናው ከሚያደርጉት ሽር ጉድ ባለፈ እንደዚህ ዓይነት ስፖርታዊ ውድድሮችን ለማዘጋጀት የሚያደርጉት ፉክክር ቀላል የሚባል አይደለም። ዓለም አቀፍ የስፖርት ሁነቶችን ለማዘጋጀት ሚሊዮኖችን አለፍ ካለም ቢሊዮኖችን ወጪ ያደርጋሉ። አገራት ውድድሩን ከማስተናገድ ባለፈ ታሪካቸውንና ባህላቸውን ጨምሮ ያላቸውን መልካም ገጽታ ለመገንባት ይጠቀሙበታል ። 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ከቀናት በፊት በማዕከላዊ አውሮፓዊቷ አገር ሃንጋሪ ተጀምሯል። በሻምፒዮናው ላይ ከ200 አገራት በላይ የተወጣጡ ከሁለት ሺህ በላይ አትሌቶች እየሳተፋ ይገኛሉ። ሻምፒዮናው ቡዳፔስት በሚገኘው ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየም በመካሄድ ላይ ይገኛል። ነሐሴ 13/2015 የሻምፒዮናው ደማቅ የመክፈቻ ስነ ስርዓት በዚሁ ስታዲየም ተከናውኗል። በመክፈቻ ስነ ስርዓቱ ላይ የሀንጋሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ቪክቶር ኦርባን፣የሀንጋሪ ፕሬዝዳንት ካታሊን ኖቫክ፣ የተርኪዬ ፕሬዝዳንት ሬሲፕ ታይብ ኤርዶጋን፣ የዓለም አትሌቲክስ ፕሬዝዳንት ሰባስቲያን ኮ፣የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ፕሬዝዳንት አሌክሳንዳር ሴፈሪንና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች መገኘታቸው ይትወሳል። እኛም ሻምፒዮናው እየተካሄደበት ስላለው ስታዲየም መረጃዎችን ልናካፍላችሁ ወደናል። ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየም የግንባታ መሰረት ድንጋይ እ.አ.አ በ2020 ተጥሎ ግንባታው የተጀመረው እ.አ.አ 2021 መግቢያ ላይ ነበር። ስታዲየሙ ግንባታው ከመጀመሩ በፊት 40 ሺህ ተመልካች እንደሚያስተናግድ ይፋ ተደርጎም ነበር። ይሁንና የግንባታው ስራ ሲጀመር በሚይዘው የተመልካች ብዛት ላይ ክለሳ ተደርጎ ስታዲየሙ 36 ሺህ ተመልካች በሚያስተናግድ መልኩ ግንባታው እንደሚቀጥል ተገለጸ። በዚሁ መሰረት የላይኛው የስታዲየም ክፍል 22 ሺህ እንዲሁም የታችኛው ክፍል 14 ሺህ ተመልካች እንዲደሚይዝ የሃንጋሪ መንግስት አስታወቀ። የስታዲየሙ ግንባታ ከእ.አ.አ 2022 አጋማሽ ዓመት በኋላ ተጠናቆ በዛው ዓመት ማብቂያ ለዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው የትኬት ሽያጭ መከናወን ጀመረ። ስታዲየሙ እ.አ.አ ሰኔ 16/2023 የዓለም አትሌቲክስ ፕሬዝዳንት ሰባስቲያን ኮን ጨምሮ ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ተመርቆ በይፋ ስራ ጀመረ። አጠቃላይ ለስታዲየሙ ግንባታ 700 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር የሚጠጋ ወጪ መደረጉንና ይህም ሀንጋሪ ለስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታ ያወጣችው ትልቁ ገንዘብ ሆኖ ተመዝግቧል። ከዚህ ቀደም ሀንጋሪ ለስፖርት መሰረተ ልማት ያወጣችው ትልቁ ወጪ ከ67 ሺህ በላይ ተመልካች ለሚያስተናግደው ፑሽካሽ አሬና ስታዲየም ሲሆን ለስታዲየሙ ግንባታ 600 ሚሊዮን ዶላር ፈሰስ እንደተደረገበት መረጃዎች ያመለክታሉ። የውድድሩ መሮጫ መም “The Crown of the Queen of Sports” የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲሆን ስያሜው የመነጨው አትሌቲክስ የሁሉ ስፖርቶች ቁንጮ ነው ከሚል እሳቤ መሆኑን ተገልጿል። ናሽናል አትሌቲክስ ሴንተር ስታዲየምን የገነቡት ‘ዛኤቭ ኢፕቶይፓሪ ዜድአርቲ’ (ZÁÉV Építőipari Zrt) ‘ማግያር ኢፒቶ ዜድአርቲ’ (Magyar Építő Zrt) የተሰኙ ተቋራጮች ናቸው። ስታዲየሙ የሚገኘው በደቡብ ማዕካላዊ ቡዳፔስት እና በአውሮፓ በትልቅነቱ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠው የዳኑብ ወንዝ ምስራቃዊ አቅጣጫ ነው። ከዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው በኋላ የስታዲየሙ የመያዝ አቅም ወደ 14 ሺህ ዝቅ እንደሚልና በተመልካቾች በኩል ያሉ ጊዜያዊ የስታዲየሙ የላይኛው ክፍል መሰረተ ልማቶች እንደሚነቀሉም ተገልጿል። የዓለም የአትሌቲክስ አፍቃሪያን በስታዲየሙ በቀጣይ ቀናት በሚካሄዱ የአትሌቲክስና የሜዳ ተግባራት ውድድሮችን በጉጉት መከታተላቸውን ይቀጥላሉ። የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናው እስከ ነሐሴ 21/2015 ይቆያል። በሃንጋሪ ቡዳፔስት እየተካሄደ በሚገኘው 19ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የአራተኛ ቀን ውሎ የኢትዮጵያ አትሌቶች የሚሳተፉባቸው ሁለት የፍጻሜ ውድድሮች ይካሄዳሉ። ከምሽቱ 4 ሰአት ከ30 የ1 ሺህ 500 ሜትር ሴቶች አትሌት ብርቄ ኃየሎም እና አትሌት ድርቤ ወልተጂ ይሳተፋሉ። አትሌት ብርቄ 3 ደቂቃ ከ54 ሴኮንድ ከ94 ማይክሮ ሴኮንድ እና አትሌት 3 ደቂቃ ከ55 ሴኮንድ ከ8 ማይክሮ ሴኮንድ በርቀቱ ያላቸው የግል ምርጥ ሰዓት ነው። በ3 ደቂቃ ከ49 ሴኮንድ ከ11 ማይክሮ ሴኮንድ የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት የሆነችው የ29 ዓመቷ ኬንያዊ አትሌት ፌዝ ኪፕዬጎን ውድድሩን የማሸነፍ የቅድሚያ ግምት አግኝታለች። አትሌቷ የ1 ማይል እና የ5 ሺህ ሜትር የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤትም ናት። በዚህ ውድድር ላይ በትውልድ ኢትዮጵያዊ በዜግነት ኔዘርላንዳዊ የሆነችው አትሌት ሲፋን ሀሰን ትወዳደራለች። ከምሽቱ 4 ሰዓት ከ42 ደቂቃ በ3 ሜትር መሰናክል ወንዶች ፍጻሜ የርቀቱ የዓለም ክብረ ወሰን ባለቤት አትሌት ለሜቻ ግርማና አትሌት ጌትነት ዋለ ይወዳደራሉ። አትሌት ለሜቻ በሰኔ ወር 2015 በፓሪስ በተካሄደው የዳይመንድ ሊግ ውድድር በ3 ሺህ ሜትር መሰናክል 7 ደቂቃ ከ52 ሴኮንድ ከ11 ማይክሮ ሴኮንድ በመግባት በኳታሩ አትሌት ሳይፍ ሰኢድ ሻሂን ለ19ኝ ተይዞ የነበረውን የርቀቱን ክብረ ወሰን በ1 ሴኮንድ ከ52 ማይክሮ ሴኮንድ ማሻሻሉ ይታወቃል። አትሌት ጌትነት 8 ደቂቃ ከ5 ሴኮንድ ከ15 ማይክሮ ሴኮንድ በርቀቱ ይግል ምርጥ ሰአቱ ነው። በውድድሩ አትሌት ለሜቻ እና የሞሮኮው አትሌት ሶፊያን ኤል ባካሊ የሚያደርጉት ፉክክር በስፖርት ቤተሰቡ ከወዲሁ በጉጉት ይጠበቃል። ኢትዮጵያ በሻምፒዮናው እስከ አሁን 1 የወርቅ፣1 የብር እና 2 የነሐስ በአጠቃላይ አራት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች።
ቡሄ እና ትውፊቱ
Aug 19, 2023 734
በአየለ ያረጋል "ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት፤ ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት" ዛሬ ማታ ለጠበል ጠዲቅ እንዳትቀር ሲሉኝ ጎረቤቴ ደብረ ታቦርን አስታወሱኝ። እኔ ባደኩበት ገጠራማ አካባቢ ዛሬን (ነሐሴ 13) ደብረ ታቦር እንለዋለን። ይህ ዕለት በአብዛኛው ኢትዮጵያ አካባቢ 'ቡሄ' በሚል ይታወቃል። የክረምት ወቅት ሦስተኛው ወርኅ ነሐሴ ነው። ቡሄ ደግሞ ከወርኅ ነሐሴ ውብ መልኮች አንዱ ነው። ትውፊታዊ አንድምታው ከክረምት ወደ ጥቢ፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከጭጋግ ወደ ወገግታ...የመሸጋገር ምኞት ጋር ይቆራኛል። "ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት" የሚባለውም ለዚህ ይመስላል። በገጠር በእርሻ ሲማስን የከረመ ለገበሬ እና በሬ ከቡሄ በኋላ እፎይታ ማግኘት ይጀምራል። የክረምቱን ከባድ ወቅት አልፎ ጳጉሜን ተሻግሮ ተናፋቂው ወርኅ መስከረም ለመድረስ ('ነይ ብራ ነይ ብራ' እንዲሉ) የቡሄ ወቅት የጉጉት ሰሞን ነው። አዲስ ዓመትን ለማየት የመሻት ምልክት ነው። በነሐሴ አጋማሽና መገባደጃ የአርሶ አደሩ ማሳ ቡቃያ ይለብሳል። ቡሄ መሠረቱ ሃይማኖታዊ ቢሆንም እንደየአካባቢው መልከ-ብዙ መንፈሳዊ፣ ባህላዊና ትውፊታዊ ክዋኔዎች አሉት። ቡሄ ታዳጊዎች ይናፍቁታል። በሃይማኖታዊ አስተምህሮው ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር (ታቦር ተራራ) ክብረ-መንግሥቱን እና ብርሃነ መለኮቱን የገለጠበት ትዕምርት እንደሆነ ሊቃውንተ- ቤተክርስቲያን ይገልጻሉ። የቡሄ ክዋኔዎች እና ስነ-ቃሎች ሆያ…. ሆዬ….!ሆ….! ቡሄ መጣ በዓመቱ፣ ኧረ እንደምን ሰነበቱ እዛ ማዶ ጭስ ይጨሳል፣ አጋፋሪ ይደግሳል፤ ... የቡሄ ዕለት ማታ ችቦ ይበራል፡፡ ሕፃናቱ ጅራፍ ገምደው ያጮሃሉ። እናቶችም ስንዴ አጥበው እና ፈትገው ዳቦ ይጋግራሉ። ሙልሙል ያዘጋጃሉ። ቀዬው በሕፃናቱ ዜማ ድባብ ይሞላል። መንደሩ በ"ሆያ ሆዬ" ሕብረ- ዝማሬ ይደምቃል። "ቡሄ ና በሉ፤ ቡሄ በሉ ቡሄ መጣ፤ ያ መላጣ፤ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ …" በሚለው። ይህ ትውልድ ተሻጋሪ ትውፊት እሴቱና ልማዱ ቢለዋወጥም ዛሬም ይከወናል። ቡሄ ትርጉሙ 'ብራ' ማለት ነው። ከሙልሙል ዳቦ በማቆራኘትም 'መላጣ" ማለት ነው የሚሉም አሉ። የቡሄ ጭፈራ በሁሉም አካባቢዎች የተለመደ ነው። ሕፃናቱ ጨፍረው ሙልሙል ዳቦ ይቀበላሉ። ሙልሙል ሲሰጣቸው ምስጋና፣ ሙልሙል ካልተዘከሩ ደግሞ የሐሜት ስነ-ቃሎችን ያስከትላሉ። ለምሳሌ በቡሄ ጭፈራ ዳቦ ከቀረበላቸው "... ሐሚና ሚና፤ ዘነዘነና የበር ዘነዘና ጌታዬን ያማ ሰው፤ እከክ ይውረሰው..." ሲሉ ሙልሙል ያልጋገረች ሴት የተገኘች እንደሆነም "የቡሄ ዕለት ያልጋገረች ሴት፤ አንድ እግሯ ከቆጥ አንድ እግሯ ከረመጥ..." ይላሉ። በነገረ ትውፊት ጽሑፎች የሚታወቁት ካህሳይ ገብረእግዚአብሔር ስለ 'ብሂለ ወራት' ከጠቀሷቸው ስነ-ቃሎች መካከል ወርኅ ነሐሴ እንዲህ ተጠቅሷል። ... " በሐምሌ እንዴት እከርማለሁ ደግሜ በነሐሴ ነፍሴን እዣለሁ በጥርሴ .... ነሐሴን በእንጥርጣሪ፣ ሐምሌን በብጣሪ ነሐሴ እግር በረቱ፣ መስከረም ዳገቱ በግንቦት አተላ፣ በነሐሴ ባቄላ ..." የቡሄ በዓል የብርሃን በዓል ማለት ነው። የብርሃኑ መገለጥ ዕለት ነው። በዚህም ነሐሴ 13 አመሻሽ ችቦ ይለኮሳል። የችቦው ትዕምርት ደግሞ አንዱ ለሌላው መካሪ አስተማሪ፣ አርዓያ፣ ምሳሌ፣ ብርሃን መሆኑን ያመላክታል። የጅራፍ ትውፊታዊ መልኩ ሁለት ዓይነት ምስጢር ይሰጠዋል። ቀዳሚው ምስጢር የኢየሱስ ክርስቶስን ግርፋትንና ሞቱን ሲሆን ሁለተኛው የጅራፍ ነጎድጓድ ድምፁ የባሕርይ አባቱን (የአብን) ምስክርነት ይወክላል። ነገረ-ሙልሙልም የራሱ ትውፊታዊ ትርጓሜ አለው። በችቦ ብርሃን ወላጆች እረኝነት የወጡ ልጆቻቸውን ለመፈለግ ሲወጡ ለልጆቻቸው በያዙት ስንቅ ይመሰላል። የሙልሙል ዳቦ ዝክሩ መተሳሰብን፣ ፍቅርንና አብሮነትን ይወክላል። ዛሬም ዳቦ የሚጋገረው ለዚህ ትውፊት ነው። ታዳጊዎች 'ሆያ ሆዬ' እያሉ ሙልሙል ዳቦ የሚጠይቁትም ከዚህ ትውፊት የመነጨ ነው። በሌላ ጎኑ ሕፃናቱ በደቀመዛሙርት፣ ዝማሬያቸው ደግሞ በ 'የምሥራች' እንዲሁም ስጦታው በምርቃት ይመሰላል። በዓለ-ደብረ ታቦር ወይም በቡሄ ትውፊታዊ ክዋኔዎች የየራሳቸው ትርጓሜ እና እሴት ቢኖራቸውም አልፎ አልፎ ከትውፊት ያፈነገጡ ክዋኔዎች ይስተዋላሉ። በዚህም ነባሩ ትውፊት ወደ ትውልድ ወግና ሥርዓቱን ሳይለቅ በቅብብል መተላለፍ እንዳለበት የሚሞግቱ ሰዎች ጥቂት አይደሉም። ለምሳሌ ጅራፍን በርችት መተካት 'የምስጢር ተፋልሶ አለው፤ ማኅበራዊ ገጽታው አይበጅም' የሚሉ ወገኖች አሉ። በሆያ ሆዬ የሚሰሙ ግጥሞች ከግብረ-ገብነት ያፈነገጡ፣ ዓለማዊ መልዕክት ያላቸው፣ ስድብ፣ ፌዝና ሥላቅ ይዘት ያዘሉ ሆነው እንደሚስተዋሉ በመጥቀስ ይህን ተግባር አጥብቀው ይተቻሉ። በሌላ በኩል በሙልሙል ዳቦ የተጀመረው እና ሃይማኖታዊ አንድምታ የነበረው የታዳጊዎች 'ሆያ ሆዬ' ትውፊታዊ ሥርዓቱን እየለቀቀ ገንዘብ መሰብሰቢያ መሆን እንደሌለበት ይነሳል። በቡሄ ምሽት በከተሞች አካባቢ የሚስተዋል የመጠጥና ስካር ድባብም እንዲሁ። ይልቁንም ለነዳያን እየዘከሩ እና እየዘመሩ በሰፈር ማኅበራዊ አብሮነት የሚያሳዩ ወጣቶችን ማበረታታት እንደሚገባ ይመክራሉ። መልካም ቡሄ!!
“አዲስ አበባ” በሞስኮ:- ኢትዮጵያን በማስተዋወቅ 27 ዓመታት የዘለቀ ጉዞ
Aug 18, 2023 457
በአየለ ያረጋል ጊዜው በሞስኮ ሰዓት አቆጣጠር ቀትሯል። ‘ጋርደን ሪንግ’ ጎዳና ማዕከላዊ ሞስኮ ከተማን (የሩስያ ርዕሰ መዲና) እንደ መቀነት ይጠመጠማል። በዚህ ጎዳና ከሚገኝ አንድ ተቋም ለብርቱ ጉዳይ ለመግባት የጎግል ካርታ ተከትዬ ከሜትሮ (ምድር ባቡር) መውጣቴ ነበር። በዚህ ቅጽበት ነበር ‘አዲስ አበባ ሬስቶራንት’ የሚለውን ስፍራ አቅጣጫ በድንገት ያስተዋልኩት። በሞስኮ ጎዳናዎች የኢትዮጵያ ሬስቶራንት ቀርቶ ኢትዮጵያዊ ማግኘት እንደ ምዕራብ ሀገራት ተራ ነገር አይደለም። ብርቅ ነው ማለት ይቀላል። እናም የኢትዮጵያ ሬስቶራንት በድንገት ማግኘቴ ለእኔ ‘ድንገቴ ፈንጠዝያ’ ሆነብኝ። ከሄድኩበት ቢሮ መግባቱን ትቼ በጎግል ካርታ እየተመራሁ ወደ ፊት ገሰገስኩ። ወደ አዲስ አበባ ሬስቶራንት። በ‘ጋርደን ሪንግ’ ጎዳና የአምስት ደቂቃ ርምጃ የጎግል ካርታው ‘ርቀቱ’ ዜሮ ሆነ። ቀና ስል በሀገሬ ሰንደቅ ዓላማ ቀለማት የቀለሙ ፊደላት አነበብኩ። የሩስኪ ቋንቋ ፊደላት ቢሆኑም ደጉ ነገር የማውቃቸው ፊደላት ነበሩ። ‘አዲስ አበባ’ ደረስኩ!! (የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሞስኮ ቢሮም ከአዲስ አበባ ሬስቶራንት ፊት ለፊት ይገኛል) ገርበብ ያለውን በር ገፍቼ ገባሁ። ከገባሁ ጀምሮ አዲስ አበባ እንጂ ሌላ ሀገር መሆኑን ዘነጋሁ። የሀበሻ ዘፈን ይደመጣል። ግድግዳው በሀበሻ ስዕላት ተሞልቷል። ጣሪያው በእንስሳት ቆዳ ተጊጧል። ባንኮኒው የብዝሀ-ኢትዮጵያ መልክ ይዟል፤ በቅርጻ ቅርጾች እና አልባሳት ደምቋል። ባንኮኒው ውስጥ ያገኘሁትን ሰው ተዋወቅሁ። ዶክተር ጥላሁን መኮንን ነው-የሬስቶራንቱ ባለቤት። የወገን ወግ ተጨዋወትን-አልፎ አልፎ ወደሩሲያኛ ቋንቋ እየተሰረቀ። በዚህ ቅጽበት ብቻ አይደለም። ሌላም፤ ሌላም ቀን እስከ ሞስኮ ቆይታዬ ድረስ። በመጨረሻም ‘አዲስ አበባ በሞስኮ’ን መጣጥፍ ለመጻፍ ወደድኩ። የእህል ውሃ ነገር ሆኖ እዚህ ቦታ ብንገናኝም ጥላሁን መኮንን የተዋጣለት የሚባል ጎበዝ ሙዚቀኛ ነበር-ፒያኒስት!! ጥላሁን እና ሞስኮ- ከልጅነት እስከ ዕውቀት ጥላሁን መኮንን ትውልዱና ዕድገቱ አዲስ አበባ ነው። የሞስኮ እና የጥላሁን ትውውቅ ግን በዕድሜው ማለዳ የተጀመረ ነው። ሞስኮን የረገጠው ገና በለጋነት ዕድሜው ነው። “በ1976 ዓ.ም ሕጻን እያለሁ ሞስኮ መጥቻለሁ። የሙዚቃ ፌስቲቫል ነበር። ስድስተኛ ክፍል ተማሪ ሆኜ ይመስለኛል” ይላል። ጥላሁን ከልጅነቱ ጀምሮ የሕጻናት ኪነት ቡድን አባል ነበር። በ1978 ዓ.ም የነ ጥላሁን የኪነት ቡድን በሀገር አቀፍ ደረጃ የነበረ ውድድርን በማሸነፍ በቀድሞዋ ሶቬት ሕብረት ለሕፃናት በዓል ተጋበዘ። ጥላሁን እና ሌሎች አራት ጓደኞቹም ኢትዮጵያን ወክለው ወደ ሞስኮ ተጓዙ። ጥላሁን ለሁለተኛ ጊዜ ሞስኮን ረገጠ ማለት ነው። “በዚህ ወቅት ሚኒስትሪ (የስምንተኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና) የተፈተንኩት እዚሁ ነበር” ይላል። ሙዚቃ የጥላሁን የልጅነቱ የነፍስ ጥሪ ነበረች። በትምህርቱም ቀለሜ ነበር። በብዙ ሙዚቀኞች እንደሚስተዋለው ወላጅ አባቱ የሙዚቃ መክሊቱን እንዳያጣጥም ሳንካ አልሆኑበትም። ከልጅነቱ ጀምሮ አይረሴ የኪነት ትውስታዎችን ሰንቋል። በዘመነ ደርግ የአብዮት ዓመታት በሕጻናት ኪነት ቡድን ውስጥ ትልልቅ ሀገራዊ መድረኮች ላይ ተሳትፏል። ጥላሁን እና ጓደኞቹ በሶማሊያው ዜያድባሬ ወረራ ጊዜ ሰራዊቱን ለማነቃቃት በሚደረጉ መድረኮች፣ በአብዮት በዓላት እና ዓለም አቀፍ በዓላት አከባብር ላይ በሕጻናት ኪነት ውስጥ ዘምሯል። በተለይም በኢሕዴሪ (የኢትዮጵያ ሕዝባዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ) ፓርቲ ምስረታ ወቅት የብሔር ብሔረሰቦችን ሙዚቃ እንዲገነዘብ ያስቻለውን ዕድል አግኝቷል። “አያሌ የአብዮት መዝሙሮችን ዘምረናል። በብስራተ ወንጌል ራዲዮ ጣቢያ የሚተላለፍ የኛ መዝሙር ነበር። ለምሳሌ ‘አይዞን ተነሺ ኢትዮጵያ፤ አለን ልጆችሽ’ የሚለው አይረሳኝም። ሁልጊዜ ቅዳሜ፣ ቅዳሜ እንቀረጽ ነበር። ትልልቅ የመንግስት መድረኮች የኛ ኪነት በድኑ ስራዎችን ያቀርባል። የዕድገት በሕብረት ዘመቻ መዝሙርና አርማ የተቀበልነው እኛ ነበርን። የሚገርምህ በቅርቡ ስለዕድገት በሕብረት ዘመቻ ታሪክ ሲተረክ የልጅነት ፎቶየን (የስምንት ወይ የሰባት ዓመት ልጅ ሆኜ) በቴሌቪዥን አይቼው ደስ ብሎኛል” ይላል። ጥላሁን የ12ኛ ክፍል ትምህርቱን በጥሩ ውጤት አጠናቆ በፒያኖ የመጀመሪያ ዲግሪውን ተቀብሏል። ለመመረቂያም ትልቅ ኮንሰርት አዘጋጅቷል። አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት ለሁለት ዓመታት አስተምሯል። የዛሬው የኢትዮጵያ ሙዘቃ ዘርፍ ማህበራት ፕሬዝዳንት ዳዊት ይፍሩን ከተማሪዎቹ መካከል ይጠቅሳል። ከአስተማሪነቱ ጎን ለጎንም ፒያኖና አኮርዲዮ በመጫወት ብዙ መድረኮች ላይ ይሳተፍ ነበር። ጥላሁን ገሰሰ፣ አለማየሁ እሸቴ፣ መሀሙድ አህመድ እና መሰል ዝነኛ ድምጻዊያን በተሳተፉበት መድረክ ሙዚቃ ተጫውቷል። የሙዚቃ ቡድን መሪ ሆኖም ነበር። በሀገር ውስጥ የህዝብ ለህዝብ መድረኮችን በማደራጀትም ተሳትፏል። ከሁለት ዓመታት የመምህርነት ቆይታ በኋላ ነበር የውጭ ትምህርት ዕድል ያገኘው። በወቅቱ ምሥራቅ ጀርመን፣ ቡልጋሪያ እና ሩስያ ምድቦች ነበሩ። ግርማ ይፍራሸዋ፣ ይገዙ ደስታ፣ መታሰቢያ መላኩና መሰሎቹ በሶስቱ ሀገራት ትምህርት የተማሩበት ዘመን ነው። ጥላሁንም ከአንድ ሺህ ተወዳደሪዎች መካከል በነበረው ውጤት ቀዳሚ ተመራጭ ሆኖ ለሁለተኛ ዲግሪ ሩስያ ተላከ። የያሬድ ሙዚቃ ትምህርት ቤት መምህራንም “እናት ሀገርህን እንዳትረሳ አደራ” ብለው ‘የኢትዮጵያ ካርታ’ ሰጥተው ላኩት። በሞስኮ ሁለተኛ ድግሪውን በከፍተኛ አፈጻጸም (በሀገሪቷ አገላለጽ ቀይ ዲፕሎማ) ይዞ ከመመረቁ ያለምንም ፈተና የሶስተኛ ድግሪ (ዶክትሬት) ትምህርት እንዲቀጥል ዕድል ተመቻቸለት። በኦርኬስትራ መሪነት (ኮንዳክተር) ሙያ ሶስተኛ ዲግሪውን ያዘ። የሩስያ ቋንቋ አስተርጓሚነት ዲፕሎማም ወሰደ። ከሞስኮ ዩኒቨርሲቲ ኦርኬስትራ ጋር ትልቅ ኮንሰርት አካሄደ። በሞስኮ ትምህርት ካልቸራል የኒቨርሲቲ መምህርነት ተቀጠረ። “አስተማሪነት በወቅቱ የኑሮ ደረጃው ከባድ ነበር” ይላል። ይህ በእንዲህ እንዳለ በኢትዮጵያ የመንግስት ስርዓት ለውጥ ተደረገ። ታላቋ ሶቬት ሕብረትም ተበታተነች። ፒያኒስቱ ጥላሁን ቀስ በቀስ ወደ ንግዱ ዓለም ተቀላቀለ። ‘አዲስ አበባን በሞስኮ’ ከፍቶ ኑሮውን ቀጠለ። አዲስ አበባ በሞስኮ አዲስ አበባ ሬስቶራንት በሞስኮ ከተማ ውስጥ በብቸኝነት አለ የሚባል የኢትዮጵያ ሬስቶራንት ነው። ጥላሁን እንደሚለው ሬስፖራንቱ በቤተሰብ የተጀመረ ነው። ከቤተሰብ ተረክቦ ‘አዲስ አበባ በሚል ስያሜ አስቀጠለው። ዘንድሮ 27 ዓመት አስቆጥሯል። የሬስቶራንቱ አገልግሎት ከምግብና መጠጥ ሽያጩ ይልቅ የኢትዮጵያን ገጽታ እና ባህል በመሸጥ ትልቅ ሚና እንደተጫወተ ያምናል። የደንበኞቹ ማንነት እና የሚቀርቡ ምግቦች አይነት ይህን ያረጋግጣል። “አዲስ አበባ የሩስያዎች ምግብ ቤት ነው። ደንበኞቻችን የውጭ ዜጐች ናቸው-በአብዛኛው ሩስያዎች። የዲፕሎማቶች ማረፊያ ነው። በተለያዩ ጊዜያት ኢትዮጵያ ውስጥ የነበሩ ሩስያዊያን መሰባሰቢያቸው ነው” ይላል። ወደ ኢትዮጵያ የሚሄዱ ቱሪስቶችም ከመሄዳቸው በፊት የኢትዮጵያን ምግብ እና ባህል የሚለማመዱት አዲስ አበባ ሬስቶራንት ነው። የኢትዮጵያን ባህላዊ ምግቦች ለማስለመድ ገጠመኞችንም ያነሳል።“አንድ ቀን እንጀራ ምግብ ታዝዘን እንጀራ ቁርጥ በጎን አቅርብንላቸውና ‘ናፕኪን’ መስሏቸው ነበር። የኢትዮጵያ ባህላዊ ምግብ መሆኑን እና እንዴት መበላት እንዳለበት አሳየናቸው። አሁን አዲስ አበባ ውስጥ የገባ ደንበኛ እንጀራ ሳይበላ አይሄድም። ምግቡ ማቀዝቀዣ ውስጥ የገባ ሳይሆን ፍሬሽ ነው። ኬሚካል የለውም። ቡናው ቀጥታ ከኢትዮጵያ እናስመጣለን-የሀረር ቡና። በኢትዮጵያ ቡና አፈላል ስርዓት ከነ ጭሱ እየተፈላ ይቀርባል። ይህን ይመርጡታል። እንጀራ፣ ስጋ ወጥ፣ የበግ ጥብስ፣ ዶሮ ወጥ… ለምደዋል” ይላል። ሶቬት ሕብረት ስትፈራርስ ከባድ የፈተና ጊዜ እንደነበር ያነሳል። በርካታ የአፍሪካ ሬስቶራንቶች ቢከፈቱም እንደ አዲስ አበባ መቀጠል ሳይችሉ እንደተዘጉ ያነሳል። ነገር ግን በአውሮፓዊያኑ አቆጣጥር 1998 ጀምሮ ሁሉም ነገር መስመር እየያዘ ስለመምጣቱ ይገልጻል። አዲስ አበባ ሬስቶራንት በሞስኮ የሚገኙ ሀበሾች ብቻ ሳይሆን መላ አፍሪካዊያን የሚገናኙበት ስፍራ ጭምር ነው። ተጠቃሽ የጥቁሮች ሬስቶራንት ነው። “ብዙ የአፍሪካ ሬስቶራንት የለም። የሩስያና የአፍሪካ ዲፕሎማሲ ማዕከል በመሆን ሚናውን እየተወጣ ነው ማለት እንችላለን። የአፍሪካ ኤምባሲዎች በሬስቶራንቱ ውስጥ ዝግጅት ያደርጋሉ። በፈረንጆች አቆጣጠር እስከ 2000 ድረስ ሬስቶራንቶች ነበሩ። አሁን የሉም። እኛ ኢትዮጵያን ብቻ ነን።” በሞስኮ የኢትዮጵያ ኤምባሲም ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን በሬስቶራንቱ ያዘጋጃል። ከኢትዮጵያ ወደ ሞስኮ ያቀኑ እንግዶች (ከፍተኛ ባለስልጣናትን ጨምሮ) ወደ አዲስ አበባ ሬስቶራንት ጎራ እንደሚሉ ይገልጻል። “ወደ ሩስያ የሚመጡ ኢትዮጵያውያን አዲስ አበባ ሬስቶራንትን ሲያገኙ ይደሰታሉ። በ2018ቱ የዓለም ኦሎምፒክ የመጡ እንገዶች ትልቅ ደስታ ነበራቸው። ብዙዎቹ ሚኒስትሮችና ዲፕሎማቶች ይመጣሉ። ይህም አለ ወይ? ይሉናል። ትንሿ ኢትዮጵያ፣ ትንሿ አዲስ አበባ ይሉናል። በጣም ይደሰታሉ። ያበረታቱናል። ከበሩ ጀምሮ አዲስ አበባ የሚለውን ሲያዩ ይደሰታሉ።” በርግጥም በተለያዩ አጋጣሚዎች ያገኘኋቸው አፍሪካዊያን ተማሪዎችና የዩኒቨርሲቲ መምራን ‘እንጀራ’ እና የኢትዮጵያውያን ‘ውዝዋዜ’ እንደሚያስደስታቸው ገልጸውልኛል። አንዳንዶቹም ከትክሻቸው ወዝወዝ እያሉ ውዝዋዜን በቀልድ መልክ ለማሳየት ሞክረውልኛል። ይህን ያወቁት ‘በሞስኮዋ አዲስ አበባ’ ነው። የሬስቶራንቱ እንግዶች ስለኢትዮጵያ መልካም ዕይታ እንዲኖራቸው ጥረት ያደርጋል። ጥላሁን የኢትዮጵያ ስም እንዲጎድፍ አይፈልግም። የኢትዮጵያ ምግብ ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ሙዚቃ ነው የሚከፈተው። ሬስቶራንቱ ኢትዮጵያ፣ ኢትዮጵያ እንዲሸት እንደሚሰራ ይናገራል። አዲስ አበባሬስቶራንት በሩሲያን መሰል በውጭ ሀገራት የተከፈቱ፣ የኢትዮጵያን ስምና ገጽታ የሚሸጡ፣ የሀገር ባህልና ወግ የሚያስተዋውቁ ባህላዊ ምግብ ቤቶችን ኤምባሲዎች ሊደግፏቸው እንደሚገባ ያምናል። “ኤምባሲዎችም ሊደግፉን ይገባል። ሬስቶራንቱ የኢትዮጵያን ኤምባሲ ነው የሚያገለግለው። የኢትዮጵያ በዓል ሲኖር ምግብ ሰርተን እናስደስታለን። ባህላችን እንሸጣለን። ዓላማችን ይህ ነው። ብዙ ሊከታተሉን ይገባል። ኢትዮጵያን እናስተዋውቃለን። ይበልጥ ማስተዋወቅ እና አስፈላጊውን ነገር መደገፍ ይገባል ብዬ አምናለሁ። የኢትዮጵያንን ባህል እንሸጣለን። ገፅታዋን እንገነባልን። ኢትዮጵየን ያላዩ እንዲያዩ እናደርጋለን። ወደ ኢትዮጵያ የሚሄዱ ሰዎች መጀመሪያ ስለኢትዮጵያ ባህልና አመጋግብ ይለምዳሉ። ጥናትም ያደርጋሉ።” ጥላሁን በሞስኮ ቆይታውና ኑሮው ደስተኛ ነው። ከሙዚቃ ሙያው መነጠሉን እንደ ዕድለ-ቢስነት ቢቆጥርም አዲስ አበባ ሬስቶራንትን ከፍቶ የሀገሩን ስም በማስተዋወቁ ግን ደስተኛ ነው። የሩስያዊያን ባህል እና የህዝቡ ማህበራዊ ውቅር ከኢትዮጵያ ጋር ተመሳስሎሽ መኖሩም ሌላው የሚደሰትበት ጉዳይ ነው። አሁን የሩስያ ዜግነትም ተቀብሏል። ሁለት ልጆችን ለአካለ መጠን አድርሷል። ሩስያዊያን ስለኢትዮጵያ ያላቸው መልካም ዕይታም ይገርመዋል። “ብዙዎቹ ሩስያዊያን የኢትዮጵያ ወዳጆች ናቸው። ለኢትዮጵያ ያላቸው ወዳጀነትና ቅርበት ሲናገሩ አታምንም። በኢትዮጵያ የነበሩ ወታደሮች ሁሉ ይመጣሉ። ስለኢትዮጵያ ህዝብ ደግነትና የዋህነት ያወሩኛል። አሁን አዲስ አበባ ደርሰው የሚመጡም አሉ። የድሮዋ አዲስ አበባ አይደለችም እያሉ ለውጡን ይተርኩልኛል። የዋህ ናቸው። በባህልም እንመሳሰላለን። ቅዳሜና እሁድ ቤተ ክርስቲያን ስሄድ እንደ ኢትዮጵያ ሰንበት ይሰማኛል። በጥምቀት በዓል ትዕይንት ልዩ ነው” ይላል። ኢትዮጵያና ሩስያ የሚመሳሰል ተከታታይ ስልጣኔ የነበራቸው ታሪካዊ ሀገራት ናቸው። ለብዙ ዘመናትም መልካም ግንኙነት አዳብረዋል። ሩስያ ብዝሀነት ያለባት ሀገር ብትሆንም ከዕድገት እንዳላገዳት ያነሳል። በኢትዮጵያ የሚስተዋለው በጎጥ እና ብሔር እርስ በርስ መናቆር ያሳዝነዋል። ለሀገር ዕድገትና አንድነት ከሩስያ መማር እንደሚገባ ያነሳል። ከምንም በላይ አንድነትን ማጠናከር ይገባል ባይ ነው።
የሩቅ ቅርቧ ሞስኮ!
Jul 27, 2023 1122
(በአየለ ያረጋል) ወትሮን ከዘንድሮ ያዋደዱ ሰማይ ታካኪ ሕንፃዎች መካከል ነው። እንደ ባሕር የተዘረጋው አርበ-ሰፊ ወንዝ እንደ ዝናር እየዞረ ይጥመለመላል። አይነተ ብዙ አያሌ ጀልባዎች በወንዙ ላይ ተሳፍረው ይርመሰመሳሉ። ሰዎች ደግሞ በጀልባዎቹ ተሳፍረው የወደዱትን ዕህል ውሃ እየተቋደሱ ይጓዛሉ። በወንዙ ግራ ቀኝ የሚገኙ ጥቅጥቅ ደን የሚመስሉ ዛፎች ሐመልማላዊ ገጽታ ለስፍራው ልዩ ውበት ደርቦለታል። ከላይ የመኪና፣ ከስር ፈጣን ባቡርን የሚሸከም ግዙፍ ድልድይ በወንዙ ላይ ተዘርግቷል። ከወንዙ ሰማይ ላይ የኬብል መኪናዎች ይከንፋሉ። የሰዎች የሐሴት ጥግ ይነበባል። ትዕይንቱ በወፍ በረር ዕይታ ሲቃኝ ዕፁብ ድንቅ ነው። ተለምዶ ከተፈጥሮ ተዛምዶ ሲታይ በአግራሞት ዕጅን በአፍ ያስጭናል። ይህ ውበት ያለው የሩቅ ቅርቧ ሩስያ ርዕሰ መዲና ሞስኮ ነው። ወንዙም ሞስኮቫ ነው! ሞስኮ አምባ ላይ ነኝ-መሀል ከተማ። ሁሉም ወለል ብሎ በሚታይበት አምባ ላይ በተተከለው አጉሊ መነፀር ሞስኮን እስከ ዕይታ አድማሷ በቀላሉ መቃኘት ይቻላል። የአያሌ ክፍል ዓለማት ስፍር ቁጥር አልባ ጎብኝዎች ስፍራው ላይ የተኮለኮሉት ለዚህ መሆኑ ነው። እኔም ወጉ ደርሶኝ ሞስኮቫ ወንዝ ራስጌ ተገትሬ ነገረ ሞስኮን ኪነ-ሕንፃ፣ ኪነ-ውበት፣ ስነ-ታሪክ መቃረም እና ሀሳብ ማውጠንጠን ቻልኩ። በሞስኮ ሰማይ ስር፤ ከሞስኮ አምባ በስተሰሜን ምዕራብ ክሬምሊን ቤተ መንግስት ግርማውን ተላብሷል። ብርቱ ውሳኔዎች መጸነሻና መወሰኛ ቁልፉ ቦታ-ክሬምሊን። ከክሬምሊን በስተቀኝ በኪነ ሕንፃው የሚወደሰው ባለወርቃማ ዕንቁላል መሰል ጉልላት የተጌጠው ቅዱስ ቤዚል ካቴድራል ይታያል። ከቀዩ አደባባይ ራስጌ! እነሆ ከሩቋ የሕልሜ ከተማ በአካል ተገኝቼ ሁለንተናዊ መልኳን በስሱ እየቃኘሁ ነው። አጋጣሚዎች የመንደር መፃዒ ዕድል ይወስናሉ-እንደ ሞስኮ። የግዙፉ ግዛተ-አፄ ሩስያ ርዕሰ መዲናነት ከታሪካዊቷ ቅዱስ ፒተርስበርግ ወደ ሞስኮ የዞረው ከአንድ ምዕተ ዓመት በፊት በፈነዳው አብዮት አጋጣሚ ነበር። አብዮቱ ለሀገሪቷ ብቻም ሳይሆን ለዛሬዋ ሞስኮም አብዮት ወለደ። ሞስኮ ከተቆረቆረች 876 ዓመት ሆኗታል። በ1147 ነበር ምስረታዋ። ስሟም እንደ መቀነስ በታጠቃት ’ሞስኮቫ’ ወንዝ የተወሰደ ነው። በሂደት ሞስኮ መባሏን አስጎብኚዎቼ አጫውተውኛል። ክሬምሊን የሞስኮ አስኳል ነው። ትርጓሜውም የከተማ ውስጥ ምሽግ ማለት ነው። የሩስያ መዲናዋ ሞስኮ ከክሬምሊን ምሽግ ተነስታ ለዘጠኝ ክፍለ ዘመናት ተጉዛለች። ሞስኮ የሮማን ግዛተ-አጼ ዘመነ መንግስትን ስነ መለኮታዊ፣ ስነ መንግስታዊና ባህላዊ አሻራዎችን በማስቀጠሏ በታሪክ ሊቃውንት ዘንድ ከሮማን እና ከኮንስታንቲኖፕል ስልጣኔ ቀጥሎ ‘ሳልሳዊት ሮም’ የሚል ተቀጽላ ስም ተችሯታል። ከሞስኮ ውብ መልኮች መካከል ‘ሰባቱ እህትማማቾች’ (The Seven Sisters) ይጠቀሳሉ። በኪነ-ሕንጻ ጥበባቸው የሚያስደንቁ ሰባት ቦታ ላይ የተገነቡ ሰባት ሰማይ ጠቀስ ሕንጻዎች ናቸው። ከአስጎብኚዎቹ እንደተረዳሁት ሕንጻዎቹ በታላቋ ሶቬት ህብረት በዘመነ ዮሴፍ ስታሊን ከ1947 እስከ 1953 (እ.አ.አ) በአራት ዓመታት ብቻ የተገነቡ ናቸው። በወቅቱ በአውሮፓ ረጅም ሕንጻዎች ነበሩ። ትዕምርታቸውም የሶሻሊስት ርዕዮተ ዓለም ዘላለማዊነት መጠቆም ነበር። በርግጥም ዛሬም የሶቬት ሕብረት ጉልህ አሻራዎች ናቸው። ዛሬም የሚሰሩ በርካታ ኪነ-ሕንፃዎች እህትማማቾችን ለመምሰል ይጥራሉ። ሰባቱ እህትማማች ለተለያዩ ተቋማት ቢሮነት፣ በአፓርታማነት እና በሆቴል አገልግሎት እያገለገሉ ይገኛሉ። ለአብነም በ1755 የተመሰረተው ስመ ጥሩ የሞስኮ ስቴት ዩኒቨርሲቲ፣ የሩስያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ሌኒንግራድስኪያ (ሒልተን ሞስኮ) እንዲሁም ዩክሬን ሆቴል (ዛሬ ራዲሰንብሉ ሞስኮ) በእህትማማቾች ሕንጻዎች ላይ ይገኛሉ። ከሞስኮቫ ወንዝ ባሻገር ሉዥንኪ ኦሎምፒክ ኮምፕሌክስ ከነሞገሱ ይታያል። ስቴዲየሙ በ2018 ሞስኮ የፊፋ ዓለም ዋንጫ ስታስተናግድ ቁልፍ ሚና ነበረው። ከስቴዲየሙ ባሻገርም 72 ሜትር የሚረዛዝሙ ወርቃማ ሚናሮዎች የተጌጠው የሞስኮ ካቴድራል መስጊድ ይስተዋላል። መልክዓ-ሞስኮ ትዕይንቶች ለዕይታ አይሰለቹም። በሞስኮቫ ታሪካዊና ባለግርማ ሞገስ ድልድዮች፣ የቀዳማዊ ፒተር(ታላቁ ፒተር) ሰማይ ጠቀስ ሐውልት፣ ጎርክና መሰል ሰፋፊ የመሃል ከተማ ፓርኮች፣ ወጥ ከፍታ ያላቸው ውብ መኖሪያ ሕንጻዎች… ብቻ መልከ-መልካም ናት። ሩስያ በ20ኛው ከፍል ዘመን መባቻ የሶቫሊዝም አብዮት ከመፈንዳቱ በፊት በቄሳሮች (ጻሮች) በሚመራ ዘውዳዊ ስርዓት ለዘመናት ተዳድራለች። የፈረንሳይ መሪ ናፖሊዎን ቦናፓርት ሞስኮን በአንድ ወቅት በቁጥጥር ስር አድርጓት እንደነበር አስጎብኚዎች ይናገራሉ። በ17ኛው ክፍለ ዘመን የነገሰው ቀዳማዊ ፒተር (ቀዳማዊ ጴጥሮስ) የሁሉም ሩስያ መስራች እና የመጀመሪያው አጼ ነው። የዘመናዊት ሩስያ መሀንዲስ ተደርጎ ይወሳል። ከቀዳማዊ ፒተር እስከ ዳግማዊ ኒኮላስ የሩስያ አፄዎች ዋና ቤተ መንግስት ቅዱስ ፒተርስበርግ ነበር። ድሕረ አብዮት የመንግስት መቀመጫ ሞስኮ ሆነች። አሁናዊ ሞስኮ በከተማ መሰረተ ልማቷና ስርዓቷ ከዓለማችን ውብ ከተሞች አንዷ ናት። የሩስያ ታሪክ ማዕከል፣ የቢሊየነሮች መደብር፣ የዝነኛ ጠቢባን፣ ሳይንቲስትና ታዋቂ ሰዎች መገኛም ናት። በመሰረተ ልማት እና በኑሮ ጥራቷም በፈረንጆቹ 2022 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከዓለማችን ምርጥ ግዙፍ ከተሞች መካከል በምርጥነት መርጧት ነበር። ሞስኮ ከ13 ሚሊዮን ህዝብ በላይ በመያዝ በህዝብ ብዛቷ ከዓለም ስምንተኛዋ ከተማ ናት። ምስጋና ለኢንተራሺያ (InteRussia Program 2023) የኢንተርሽፕ ስልጠና ይሁንና የሩቅ ቅርቧን ሞስኮ በቅጡ ተዘዋውሮ የመጎብኘት፣ ከጥበብ ድግሷ የመቋደስ፣ በውበቷ የመመሰጥ፣ ከታሪኳ የመቃረም ዕድል አገኘሁ። የሩስያው ዜና አገልግሎት ‘ስፑትኒክ’ ከአጋሮቹ ጋር ባመቻቸው በዚህ ፕሮግራም ከአፍሪከ ሀገራት 10 ወጣት ጋዜጠኞች ተሳትፈናል። እኔ ከሌሎች በተለየ ለሩስያ ቀረቤታ ያለኝ ያህል ይመስል ነበር። ምክንያቱ ደግሞ የታላቁ ሩስያዊ ደራሲ አሌክሳንደር ፑሽኪን ቅድመ አያት በቀዳማዊ ፒተር ዘመን በጀግንነቱ በተመለመለው አብርሐም ሃኒባል ኢትዮጰያዊ መሆኑ ነው። በርግጥም ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ከሩስያ ጋር ያላቸው ታሪካዊ ግንኙነት በ1960ዎቹ የተጀመረ ሲሆን የኢትዮጵያ ግን ብዙ ዘመናት ወደኋላ ይርቃል። ሩስያን በስማበለው የመናፈቅ ጠኔም ነበረብኝ። ለምን ሩስያን ለማየት ናፈቅሁ? ከታሪካዊ አጋጣሚዎች ተነስቼ ለሩስያ አወንታዊ ስሜት ካደረብኝ ውሎ አድሯል። በዘመናት ሸለቆ በዘለቀ የኢትዮ- ሩስያ ጽኑና ጥልቅ ወዳጅነት እና የሁለቱ ሀገራት የታሪክ ሂደቶች ተመሳስሎሽ ጥቂት ግንዛቤ ነበረኝና። ሁለቱ ጥንታዊ ሀገራት በዘውዳዊ ስርዓት (ሩስያ በቄሳር፤ ኢትዮጵያም በአጼዎች) ለዘመናት ተዳድረዋል። በየዘመናቱ አያሌ ኅይሎች ሁለቱንም ሀገር በተደጋጋሚ አጥቅተዋል። በአንድ ክፍለ ዘመን ውስጥ (ዓመቱ ቢለያይም) የሁለቱ ሀገራት ባላባታዊ ስርዓት በስር ነቀል አብዮት ተገርስሷል። አብዮቱ የንጉሳዊያን ቤተሰቦችን ለስደትና ለጉዳት በመዳረግ ተመሳሳይ ዕጣ ፈንታ አድርሷል። ድሕረ አብዮት የእርስ በርስ ደም አፋሳሽ ዕልቂት ሩስያ በቦልሸቪክ እና መንሸቪክ (Bolshevik and Menshevik)፤ ኢትዮጵያ ደግሞ በቀይና ነጭ ሽብር መልከ ብዙ ግፎች አስተናግደዋል። የሁለቱ ሀገራት ነገስታት ግንኙነት ለመመስረት ፅኑ መሻት እንደነበራቸው ይወሳል። ቀዳማዊ ፒተር ወደ ኢትዮጵያ መልክተኛ ለመላክ ሞክሮ እንዳልተሳካለት ይወሳል። ከኢትዮጵያ ወገንም ዳግማዊ አጼ ቴዎድሮስ ታሪካዊ የ’ሴቫስቶፖል’ መድፍን ስያሜ የሰጠው በክርሚያ ጦርነት መነሻ ነበር። አጼ ዮሐንስ አራተኛ በተመሳሳይ በተለይም ከክርስትና እምነት ጋር በተያያዝ ከሩስያ ጋር ጥብቅ ወዳጅነት ለመመስረት ፍላጎት እንደነበራቸው ይወሳል። በመጨረሻም በ19ኛው ክፍል ዘመን መገባደጃ በዳግማዊ አጼ ምኒልክ እና በቄሳር ዳግማዊ ኒኮላስ ዘመነ መንግስት ይፋዊ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ተወጥኗል። በተለይም በ1880ዎቸ መጨረሻ ማሽኮቭ፣ ኤሊሴቭና ሌዎንቴቭ፣ አሌክሳንደር ቭላቶቪችና መሰል ሩስያዊ ተጓዦችና የስነ መልክዓ ምድር አጥኝዎች ወደ ኢትዮጵያ መምጣት የሀገራቱን ግንኙነቱን ፈር አስይዟል። የኢትዮጵያና የሩስያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት ትብብርም በ1880ዎቹ ጀምሮ እየተጠናከረ መምጣት ለባህል ዲፕሎማሲው የማይናቅ ሚና ነበረው። በአድዋ ድል ማግስት በ1897(እ.አ.አ) ሩስያ ኤምባሲዋን አዲስ አበባ ከፈተች። በ1895(እ.ኤ.አ) ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ምድር ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ሩስያ የዲፕሎማሲ ልዑክ በፊታውራሪ ዳምጠው ከተማ (የራስ ደስታ ዳምጠው አባት እና በኋላም በአድዋ ጦርነት የተሰዉ) የተመራ ልዑክ ልካለች። ፊታውራሪ ዳምጠው የሩስያ አጼዎች መናገሻ በሆነችው ቅዱስ ፒተርስበርግ ሲደርሱ ደማቅ መስተንግዶ ተደርጎላቸው ለአንድ ወር ቆይተው ቀጣይ ግንኙነት መሰረት መጣል ብቻ ሳይሆን ለአድዋ ጦርነት ወሳኝ ድጋፍ ሰንቀው ተመልሰዋል። በኋላም በኒኮላይ ሌዎንቴፍ (በኋላ ደጃዝማች) መሪነት አድዋ ጦርነት ላይ አይተኬ ሚና የተጫወቱ ከ40 በላይ የቀይ መስቀል በጎ ፈቃደኞች እንዲመጡ አስችሏል። በበርሊኑ ጉባዔ መላው የአውሮፓ ኅያላን አፍሪካን ለመቀራመት ሜዴትራኒያንን ሲያቋርጡ ሩስያ ግን በተዘዋዋሪም ቢሆን ከኢትዮጵያ ጎን ቆማ ደገፋለች። ይህ የሩስያ ቀዳሚው ውለታ ነበር። አጼ ምኒልክ በአውሮፓዊያኑ 1898 በፒዮተር ቫስሎቭ የሚመራ የሩስያ ልዑክ ደማቅ አቀባበል አደረጉ። ጄኔራል ኮንስታንቲን ሊሸን የተባሉት በኢትዮጵያ የመጀመሪያው የሩስያ አምባሳደር (በወቅቱ ካውንስለር) አዲስ አበባ ውስጥ ሕይወታቸው እስኪያለፍ ድረስ የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት በጸና መሰረት ላይ እንዲቀጥል አይተኬ ሚና ተጫውተዋል። መካነ ቀብራቸው አዲስ አበባ ይገኛል። በርግጥ የዳግማዊ ምኒልክ እና የዳግማዊ ኒኮላስ ግንኙነት ሙሉ መተማመንና ልባዊ ወዳጅነት እንደነበረው የተለዋወጧቸው ደብዳቤዎች ዋቢ ናቸው። የደስታና ሀዘን ስሜቶችን ተጋርተዋል። ለአብነትም ዳግማዊ ኒኮላስ በራስ መኮንን ድንገተኛ ሕልፈት ማዘናቸውን የሚገልጽ ደብዳቤ ልከዋል። በተመሳሳይ ዳግማዊ ምኒልክ በጦርነት በሩስያዊያን ላይ የደረሰ ጉዳትን አስመልክቶ በጀኔራል ሊሸን በኩል የማጽናኛ ሀዘናቸውን ልከዋል። ሀዘን ብቻም ሳይሆን ተጎጂዎችን ለመደገፍ በሚል ለሩስያ ቀይ መስቀል ገንዘብ ድጋፍ ልከዋል። ‘የአጼ ምኒልክ የውጭ ሀገር ደብዳቤዎች’ በተሰኘው የጳውሎስ ኞኞ መጽሐፍ እንደተጠቆመው ዋና ፍሬ ነገሩ ይነበባል። “ሰላም ላንተ ይሁን፡፡ በሩቅ አገር የመስኮብ መንግሥት ልጆች ለንጉሣቸውና ለአገራቸው ደማቸውን በማፍሰሳቸው ብዙ አሳዘኑኝ፡፡ ጥቂትም እንኳን ቢሆን ለእነዚያ ለተጐዱት ልጆች ለመርዳት ብዬ ከዚህ ደብዳቤ ጋር አንድ አክሬዲልዩን ቼክ ስለመቶ ሺ ፍራንክ ልኬልሃለሁና ይህንን ቼክ ከመልካም ምኞቴ ጋር ለመስኮብ የቀይ መስቀል አለቃ እንድታደርስልኝ ይሁን።ይህን አሁን በመስኮብ መንግሥት የተነሳውን ጦር ጠላታቸውን አሸንፈው በቶሉ እንዲያልቅ እጅግ የከበሩ ታላቅ ወዳጃችን የመስኮብ መንግሥት ንጉሠ ነገሥት በጤና በሀብት እንዲያኖራቸው፣ለመስኮብ መንግሥት ሰላምና ረፍት እንዲሰጥ እግዚአብሔርን እንለምናለን”፡፡ የሁለቱን ሀገራት መልክዓ ምድራዊ ርቀት ያልገደበው መተሳሰብ ስሜት ያንጸባረቀ፤ የጋራ ዕጣ ፈንታ እንዳላቸውም የሚያመላከት ይመስላል። አጼ ምኒልክ ከሩስያ በስተቀር ኢትዮጵያ ሁነኛ ወዳጅ እንደሌላት እስከ መግለጽ ደርሰው ነበር። ይህ የኢትዮ-ሩስይ ወዳጅነት እስከዛሬ ሳይዛነፍ በመልካም ትብብርና መደጋገፍ ቀጥሏል። ሩስያዊያን ደጃዝማች ባልቻ ሆስፒታልን ጨምሮ በተቋማት ግንባታ አሻራቸውን አሳርፈዋል። በሁለተኛው የፋቪስት ኢጣሊያ ወረራ ወቅትም በኢትዮጵያ ላይ ማዕቀብ ሲጣል የተቃወመች ሩስያ (የወቅቱ ሶቬት ህብረት) ነበረች። ከነጻነት በኋላም በሶቬት ህብረት ሩስያና ኢትዮጵያ ወዳጅነት ዳግም ተጠናክሯል። በአጼ ኅይለስላሴ ዘመነ ምነግስት በሰው ሀብት ልማትና መሰረተ ልማት ላይ መልካም የትብብር ጅምሮች ነበሩ። በዘመነ ደርግ ደግሞ ከፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም ጋር ተዳምሮ ሁሉን አቀፍ ትብብር ነበር። በዘመኑ ለኢትዮጵያ ሉዓላዊነትና የግዛት አንድነት መጠበቅ ትልቅ ሚና ተጫውተዋል። ከ20 ሺህ በላይ ኢትዮጵያዊያን በቀድሞዋ ሶቬት ህብረት ዘመን የነጻ ትምህርት ዕድል አግኝተው ትምህርታቸውን ተከታትለዋል። እነዚህ ጥልቅ ታሪካዊና መንፈሳዊ ትስስሮች ሩስያን እንድናፍቅ ያደርገኛል። በሌላ በኩል ስለሩስያ ትልቅ ክብር እንዲኖረኝ ያደረገኝ በቁንጽል ንባቤ እንዲሁም በየዘመናቱ ሩስያ የተማሩ ኢትዮጵያዊያን ስለሩስያ የሚሰጡት ፍቅርና አክብሮት ነበር። ለአብነትም ፊታውራሪ ተክለሐዋሪያት ተክለማርያም ይጠቀሳሉ። በራስ መኮንን ቤት ያደጉት ፊታውራሪ ተክለሀዋሪያት ገና በልጅነታቸው (በ19ኛው ክፍል ዘመን መጨረሻ) በራስ መኮንን አደራነት እንዲማሩ በሚል ከአንድ ሩስያዊ ጋር ወደ ቅዱስ ፒተርስበርግ አቅንተው ያደጉ፣ የተማሩና የኖሩ እንዲሁም በኋላ በዘመናዊት ኢትዮጵያ ፖለቲካና ሀገር መንግስት ግንባታ ሂደት ትልቅ ሚና የነበራቸው፣ ከቀደምት ዘመናዊ ትምህርት ፈር ቀዳጆች መካከን የሚጠቀሱ ጉምቱ አሰላሳይ ምሁር ሰው ናቸው። በሩስያ እናቶች ቤት ያደጉት እነሁ ሰው ‘አውቶባዮግራፊ’ በተሰኘው ግለ ታሪክ መፅሐፋቸው እንደከተቡት ስለሩስያ ህዝብ ፍቅርና የሀገሩ ኅያልነት አንስተው አይጠግቡም። “ሩስያ ሁለኛ ሀገሬ ናት። ለእኔ የዋሉልኝ ውለታ መቼም ልረሳው አልችልም። ሩሲያኖች ሐሳባቸው ሰፊ፣ ሥራቸው ጠንካራ ነው: በማንኛውም ሙያ የሚያሽንፋቸው ኃይል ሊኖር አይችልም"ብለዋል። የቀድሞ ተማሪዎችም ቢሆኑ ስለሩስያ ህዝብ ያላቸው አክብሮት ልዩ ነው። በሩስያ አይረሴ ትዝታ የቋጠሩበት፣ ወጣትነታቸውን ያጣጣሙበት፣ ታሪክ፣ ስነ ጥበብና ስነ ጽሁፍ ከፍታቸው የሚደንቃቸው፣ የሀገር ፍቅር ስሜታቸው የሚያስቀናቸው ናቸው። ካነጋገርኳቸው መካከል ደራሲና ሃያሲ አያልነህ ሙላቱ፣ አንጋፋው ዲፕሎማት በላይ ግርማይ፣ የእርሻ ባለሙያው አለማየሁ አሊ እና ዕውቁ ሰዓሊ መዝገቡ ተሰማ የሩስያ አየር ጸባይ ፈተናን ባይዘነጉም የሰዎችን ፍቅር፣ የሀገሩን ጥበብና ኅያልነት ግን አውስተው አይጠግቡም። ዛሬም ይናፍቃቸዋል። የተናፋቂዋ ሞስኮ ልዩ መልኮች የሚዲያ ትርክቶች እና የሞስኮ ዕውነታ ሞስኮ ከመምጣቴ ጥቂት ቀናት በፊት ዋግነር ቅጥረኛ ወታደሮች ሞስኮን ሊቆጣጠር እያመሩ ነው፤ የመንግስት ወታደሮችም በሞስኮ ጎዳናዎች እየተውረበረቡ ነው የሚለው ዜና የምዕራባዊያን ሚዲያዎች ሰበር ወሬ ነበር። ከአዲስ አበባ-ዶሞዴዶቮ አየረ ማረፊያ ደርሼ፣ ወደ ማረፊያ ሆቴል ሳመራ ያየሁት መልክ የጠበቅሁት አልነበረም። ወሬና ዕውነታው ፍጹም የተለየ ነበር። በሞስኮ ጎዳናዎች ቅንጡ ተሽከርካሪዎች፣ ጥቅጥቅ ጫካ የሚመስሉ ዛፎች፣ ቆነጃጅት ልጃገረዶች እንጂ ወታደር አልነበረም። (ከዚያም በኋላ አላየሁም)። ይልቁኑም በዕለቱ የገጠር ሰዎች (አርሶ አደሮች) ለመዝናናት ወደ ከተማ እየመጡ በመሆኑ ሞስኮ የቅንጡ መኪኖች ትራፊክ መጨመሩን ሰምቼ፤ የሀገሬን አርሶ አደር ሕይወት ሀሳብ አቃጭሎብኝ በቁጭት አስፈግጎኛል። የሞስኮ መልክና የመጀመሪያ ግምት ልዩነት የእኔ ብቻ ሳይሆን የሌሎች አፍሪካዊያን ጓዶቼም ትዝብት ነበር። የዚምባብዌ ፕሬስ ድርጅት ጋዜጠኛ ሞቢሌ ችሊ ለረጂም ዓመታት በተለያዩ የምዕራባውያን የቴሌቪዥን መስኮቶች ስለሩስያ የሰማሁት ነገር አሉታዊ ነበር። በአካል ሩስያ መጥቼ ያረጋገጥኩት ነገር ቢኖር ግን የሩስያዊያን በጎ ማንነታቸው አለመተረኩም ነው” ይላል። የሞስኮ ሰላማዊነትና የንግድ ማዕከላት ድምቀት ጦርነት ውስጥ ያለች ሀገር አትመስልም። ‘እውን በሁለንተናዊ ማዕቀብ ያለች ሀገር ናት’ አሰኝቶኛል። የሶስት ሳምንታት ቆይታዬ ሞስኮ ቱሪስቶች መነሃሪያ መሆኗን ታዝቢያለሁ። በየመዝናኛ ቦታዎችና ታሪካዊ ስፍራዎች የሚርመሰበስ የተለያዩ ሀገራት ጎብኚዎች ብዛት የትየለሌ ነው። የአንድ ወገን የዓለም የሚደያ ቅኝት ወደ ብዝሀ ድምጽ ዓለም መለወጥ የሚሻበት ወቅት መሆኑን አፍሪካዊያን ጓደኞቼ ሲነግሩኝ ነበር። ተዓምረኛዋ ሞስኮ መልክዓ-ሞስኮ አጃይብ ነው። ‘አዲስ እረኛ’ እንዲሉ ከተማዋ ከመግባቴ በከተማዋ ስልጣኔ በመደመም ያስደነቀኝን ነገር ሁሉ በፎቶ ለማስቀረት እየሞከርኩ ነበር። ጠለቅ ባልኩ ቁጥር ግን አግራሞቴ እየጨመረ መጣና ሰለቸሁ። በየዕለቱ የሚወለወሉ ጎዳናዎች፣ የኪነ ሕንፃ ጥበብ የፈሰሰባቸው አፓርታማዎች፣ በየፊናው የሚስተዋሉ ታሪካዊ ስፍራዎች፣ ድልድዮች፣ አዕዋፍት የሚርመሰመሱባቸው አረንጓዴ ስፍራዎችን ያስቀናሉ። ሞስኮ ተፈጥሮን፣ ታሪክን፣ ትውፊትንና ስነ ጥበብን አሰናስላ ያቃፈች ከተማ ናት። የምድራዊ ገነት ሽርፍራፊ ሳትሆን አትቀርም። አያሌ ታሪካዊና ውብ ከተሞች ሊኖሩ ቢችሉም እንደሞስኮ በተፈጥሮ የታደለ፣ በታሪክ የከበረ፣ በጥበብ የተቸረ ኩሉ በኩለሔ አይነት ከተማ ማግኘት ሊያዳግት ይችላል። ሞስኮ የሩስያ የባህል ሙዳይ፣ ሞስኮ የስነ ጥበብ ማዕከላት ማህደር፣ የቅርስና ታሪክ ቤተ መዘከር፣ የፖለቲካና የምጣኔ ሀብት ማዕከል ናት። ሞስኮ በስርዓትና በቅጥ የተገነባች፣ በመገንባት ላይም ያለች፣ ትናንቷን በቅጡ የምትዘክርና የምታድስ ከተማ ናት። ዕጹብ ድንቅ ኪነ ሕንጻ ጥበብ ያላቸው የሞስኮ አብያተ ክርስቲያናት ብዛት ይገርማል። የቀዩ አደባባይ ወርቃማ ሽንኩርት ቅርፅ ጉልላት ተምሳሌትነት የያዙ አብያተ ክርስቲያናት የሞስኮ ድምቀት ናቸው። በየስጦታ ዕቃ ቤቶች እንደ ብሔራዊ ትዕምርትነት ይሸጣሉ። ኪነ ጥበብ እና ሩስያ በታሪክ ዘውድ እና ጎፈር ይመስላሉ። በ10ኛው ከፍለ ዘመን ክርስትና እምነት መስፋፋትን ተከትሎ መፋፋት የጀመረው የሩስያ ኪነ ጥበብ በቀዳማዊ ፒተር ዘመን ጀምሮ ያለማቋረጥ እምርታ እያሳየ ቀጥሏል። እናም በዘመናት የሩስያ ኪነ ጥበብ ቱርፋቶች ከመላው ዓለም የጥበብ ቤተሰቦችና ጎብኚዎችን መስህብ ሆነዋል። ሩስያዎች ደግሞ ታሪካቸውንና ባለታሪኮችን ያከብራሉ፤ በቅጡም ይዘክራሉ። ካስነደቁኝ የሞስኮ የኪነ ጥበብ ማዕከላት መካከል ትሬትያኮቭ ጋለሪ (Tretyakov Gallery) አንዱ ነው። 11ኛው እስከ 20ኛው ክፍለ ዘመን የነበሩ ከ180 ሺህ የሩስያ ስዕላት፣ ቅርጻ ቅርጾችና ግራፊክ ስራዎች የሩስያ የስነ ጥበብ ስራዎችን ያቀፈ ተቋም ነው። አስጎብኚዎቹ እንደሚሉት ጋለሪው ከ150 ዓመታት በፊት ፓቬል ትሬትያኮቭ በተባለ አንድ ባለጸጋ የስዕል ስብስቦች ቤት የነበረ ሲሆን በኋላ በባለቤቱ ፈቃድ ለመንግስት ተላልፎ የሩስያ የስዕል ጥበብ ማህደርነት ተደራጅቶ የዛሬውን ቅርጽ ይዟል። ጋለሪው የሩስያን ጥንተ ነገር፣ የሶቫሊስት እሳቤን፣ ተፈጥሮን፣ ስነ መለኮትን እንዲሁም ነገን በሚተነብዩ ጠቢባን የተሰሩ ኦርጅናል ስራዎች አቅፏል። የመላው ሩስያዊያን ኤግዚቪሽን ማዕከል (All Russian Exhibition of Achievements of National Economy) ሌላው አጃይብ ያሰኘኝ ተቋም ነው። በ1940ዎቹ የተገነባ በስፋት፣ በግንባታ ጥራትና ስነ ውበት ለመግለጽ ቃላት የሚያንስበት ማዕከል ነው። የቀድሞዋ ሶቬት ሕብረት ታሪክና ባለታሪኮች፣ የሀገሪቷን የቴክኖሎጂ ምጥቀት ቁልጭ ብሎ ይታያል። የሩስያ የሥነ ሕዋ ቤተ መዘከርም ከዚሁ ማዕከል ፊት ለፊት ይገኛል። ለዚህም ይሆናልይህ ስፍራ በጎብኚዎች ማዕበል ሲታመስ የሚውል ነው። ሞስኮ ዕልቆ መሳፍርት የሌለው የሐውልት ከተማም ናት። በሞስኮ ጎዳናዎች፣ አደባባዮች፣ በኪነ ጥበብ ማዕከላትና በንግድ ማዕከላት አካባቢዎች ሁሉ መልከ ብዙ የቅርጻ ቅርፅ ጥበብ ከፍታን የሚዋጁና ሞገስ ያላቸው ሐውልቶች ማየት ብርቅ አይደለም። ይህም የሥነ ጥበብ ከፍታቸውን ብቻ ሳይሆን የሩስኪዎችን የሀገር ፍቅር፣ ታሪክና ባለታሪክ የማክበርና የመዘከር ጽኑ መሻትን የሚያሳይ ነው። እናም ከሩስያ ሀገረ መንግስት ምስረታ ጀምሮ አሻራ ያላቸው መሪዎች፣ ጠቢባን፣ ሳይንቲስቶችና ምሁራን ስራቸውን የሚመጥን መታሰቢያ ቆሞላቸዋል። በርግጥ ሐውልት ብቻ ሳይሆን በጎዳናዎች፣ በሜትሮ (በከተማ ባቡር) ጣቢያዎች፣ በተቋማት ስም መሰየምም የተለመደ ነው። የሞስኮ ጎዳናዎች የአዘቦት ትዕይንቶች መቼስ የጎዳናዎች ስፋት፣ ጥራት፣ ውበት፣ የመሬት ስር እግረኛ ማቋረጫዎች፣ አረንጓዴያማ ተክሎች ለዐይን አይጠገቡም። ዋው! ብሎ ማለፍፍ ይቀላል። ከጎዳናዎች ውበት ባሻገር ግን መሰረተ ልማቱ ከቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን የተቆራኘበት ከፍታ ጥግ ግሩም ነው። ሞስኮ ዲጂታላይዜሽን የአገልግሎትና ንግድ ስራና ኑሮን ያቀለለባት ከተማ ናት። ሞስኮ ውስጥ ከግለሰብ እስከ መንግስት ሕንጻዎች፣ መሰብሰቢያ ስፍራዎች፣ ጎዳናዎች በደህንነት ካሜራ አላቸው። ከ70 በመቶ በላይ የጸጥታ ችግፍ የሚፈታው ካሜራዎች ከቀረጹት ግብዓትን በመጠቀም ነው። በሞስኮ ጎዳናዎች የሲጋራ ጭስና አጫሽ ማየት አያስደንቅም። ሴትና ወንዱ፣ ወጣትና ሽማገሌ ብሎ በዕድሜና ጾታ ሳይገደብ ያጨሳል። ይህ ወቅቱ ክረምት ስለሆነ (በእነርሱ የፀሐይ ወቅት) እንጂ በበጋ የጭስ ምጣኔው በጣም እንደሚጨምር ሰማሁ። ግን ህዝቡ ስርዓት አለው፤ በማይጨስበት ክልክል ስፍራ ማንም አያጨስም። በኤሌክትሪክ ኅይል የሚሰሩ አይነተ ብዙ መንቀሳቀሻዎች (ስኮተርና ስኬች)፣ ባይስክሎች እና ሞተርሳይክሎች የሞስኮ መለያዎች ናቸው። የሞስኮ ከተሜዎች አጫጭር ርቀት ለመሄድ ከባስና ሜትሮ(ባቡርይ ይልቅ እነዚህን መንሸራቻዎች ይመርጣሉ። እነዚህ መሳሪያዎች የራሳቸው ፓርኪንግስ ስፍራም አላቸው። ከሌሎች ተከራይቶ ተጠቅሞ መመለስ ይቻላል። በተባበሩት መንግስታት የመሰረተ ልማት ጥራት ተመራጭ ከተሞች መካከል የተጠቀሰችው ሞስኮ፤ ‘የስማርት ሲቲ’ ምሳሌም ሳትሆን አትቀርም። ሩስያዊያን ባህሪያቸው ይገርማል። አብዝቶ ጭምቶች ናቸው። በፍጥነት ይጓዛሉ። ተሰባስበው አያወሩም። ቢያወሩ እንኳ ሳቅ፣ ሁካታ፣ ጫጫታና ጩኸት አያሰሙም። ሽማግሌ ባለበት መድረክ እንደማያወራ የሀበሻ ልጅ እንቅስቃሴያቸው ስነ ስርዓታዊ ነው። በሞስኮ ሜትሮ ውስጥ ቡድን ጮኸ ብሎ የሚስቁና የሚጫወቱ ሰዎች ካሉ ምናልባት እኛ አፍሪካዊያን ነን። በዚህ ርዕሰ ጉዳይ ዙሪያ ከአናስታሲያ ጋር ስናወራ (በኢትዮጵያ አየር መንገድ የሞስኮ ቅርንጫፍ ቢሮ ባልደረባ ናት) “እኛ ሩስያዊያን ሲያዩን ቁጡ እንመስላለን። ብዙ ደማቆች አይደለንም። ግን ከሳቅን ዕውነተኛ ሳቅ ነው የምንስቀው። አናስመስልም” ነበር ያለችው። ከሌሎች ኢትዮጵያዊያን ያረጋገጥኩትም ነገር ቢኖር ሩስኪዎች ከወደዱ ወደዱ ነው፤ ማስመሰል አያውቁም። ሩስኪዎች ዝምታ ብቻ ሳይሆን ሰው ላይ ትኩረት አያደርጉም። ከወጣት እስከ ሽማግሌ ጆሯቸው ላይ ማዳመጫ ሰክተው፤ ሌሎቹ ስልካቸው ሏይ አፍጥጠው ይንቀሳቀሳሉ። የሩስያዎች የስነ ጽሁፍ እና የስነ ጥበብ አሻራ መዳበር መሰረት የሆነው የማንባብ ባህላቸው ዛሬም አልጠፋም። በትራንስፖርት ቦታዎችን ጨምሮ ሩስኪዎች መፅሐፍትና ጋዜጣ ያነባሉ። በሆቴሎች ሳይቀር እንደ ቤተ መፃሕፍት በየሕንጻ ወለሎች ኮሪደር ትልልቅ የመፅሐፍት መደርደሪያዎች ተቀምጠዋል። የሆቴል ደንበኛ የፈለገውን መፅሐፍ ወስዶ አንብቦ መመለስ ይችላል። በጎዳናዎችና ሜትሮ ጣቢያዎች ሙዚቃ እየተጫወቱ ገንዘብ የሚሰጣቸው ሰዎች በብዛት ይታያሉ። ሰዎች ገንዘባቸውን የሚለግሱት የሙዚቃ ጥበቡን አድንቀው ወይስ ድጋፍ ጠያቂዎችን ተቸግረዋል በሚል ለልመና የሚሰጥ ይሆን የሚለውን አላረጋገጥኩም። ሌላው የሞስኮ ቆይታዬ አይጠበቄ ክስተት የቀኑና ሌሊቱ ርዝመት ወይም የፀሐይ ሥርቀትና ግባት ሁኔታ ነው። ሰዓቱ ከኢትዮጵያ ጋር ተመሳሳይ ነው። በክረምትና በጋ ባህሪያት ግን የተገላቢጦሽ ነን። እናም ወቅቱ ክረምት መሆኑ ትልቅ አጋጣሚ ነበር። የሩስያ መለያ የሆነው አስቸጋሪ ቅዝቃዜ በበጋ ወቅት እንጂ በክረምት የለም። በክረምት ወቅት የሞስኮ ፀሐይ የምትጨልመው ዘግይታ፣ የምትሠርቀው ደግሞ ፈጥና ነው። ሞስኮ ብርሃኗ ሰፊና ረጅም ነው። ለምሳሌ አዲስ አበባ ዶሮ በሚጮኸበት ከሌሊቱ አስር ሰዓት የሞስኮ ሰማይ የአህያ ሆድ መስሏል። አስር ሰዓት ተኩል ገዳማ የሩስያ ፀሐይ በሞስኮ ውብ ሕንጻዎች ላይ ጮራዋን ትፈነጥቃለች። ይህ ብቻ አይደለም። አዲስ አበባ ሕልም ላይ በሆነችበት፣ የአራዳ መንገዶች ኦና በሆኑበት ከምሽቱ አራት ሰዓት ላይ ሞስኮ ምሽት ዓይን መያዝ ይጀምራል። ወደ ቤት ለመግባት የሚደረግ የሞስኮ ሰላማዊ ትርምስምስ ይጀምራል። በርግጥ የሞስኮ ሱፐርማርኬቶች 24 ሰዓት ክፍት ናቸው። በክረምት የሞስኮ ፀሐይ ሌሊት ወጥታ ሌሊት ትጠልቃለች። አንዱ ግርምቴ ነው። በተለይም ከሌሊቱ አስር ሰዓት ከእንቅልፌ ስባንን መስኮት ከፍቼ ቴራስ ላይ ቁጭ ብሎ ትዕይንተ ሞስኮን መቃኘት አስደስቶኛል። ሰዓት አክባሪው ‘ሜትሮ’ የስርቻው ቤተ መንግስት ሜትሮ ማለት በሩስያኛ ከመሬት ግርጌ (ስርቻ) ወይም ባንቧ ማለት ነው። ይሄውም ከመሬት በታች በጥልቀት ተቆፍሮ የተገነባው የከተማ ውስጥ ባቡር መጠሪያ ቃል ነው። ሜትሮ የሞስኮ ሁለንተና ነው። በዕለታዊ ኑሮ ውስጥ በስፋት የሚወሳ ቃል ነው። የሜትሮ ተዘውታሪነት በመጓጓዣነት የአንበሳውን ድርሻ መያዙ ብቻ አይደለም። መሰረተ ልማቱ የተገነባበት መንገድ ከአገልግሎት ባሻገር ለከተማዋ ቅርስና መስህብ እንደሚሆን እሙን ነው። የሞስኮ ህዝብ ሜትሮን ከመኪናው ወይም ከከተማ ባስ ይልቅ በብዙ እጥፍ ይመርጠዋል። ምክንያቱም ሜትሮ በአማካይ 90 ሰከንዶች ልዩነት እየተጥመለመለ ይደርሳል። በመሳፈሪያ ቦታ የቆመን ተሳፋሪ በሙሉ አንዴ ጎርሶት እልም ብሎ በ90 ሰከንድ ልዩነት ሌላው ይከተላል። አገልግሎት ከጀመረ 70 ዓመታት ያስቆጠረው የሞስኮ ሜትሮ ሰዓት አክባሪና አስተማማኝ የትራንስፖርት ድርጅት ነው። ከመሬት በታች የሚርመሰመሰው ሜትሮ አስደናቂው ነገር መስመሮችን እና መሳፈሪያ ጣቢያዎች ግንባታ ጥራትና ውበት ነው። የሜትሮ ስነ ሕንጻ ጥበብ ግሩም ነው። ሜትሮ በንጹህነቱ፣ በስነ ጥበባዊ ውበቱ፣ በአጠቃላይ ገጽታው የተነሳ ‘የስርቻው ስር የሰፊ ህዝብ ቤተ መንግስት’ ይሰኛል። ሰዓት አክባሪው የስርቻው ቤት መንግስት ያልኩትም ለዚህ ነው። ታሪካዊ ዕውነታዎች እንደሚያስረዱት የመጀመሪያው ሜትሮ መስመር አገልግሎት ፕሮጀክቶች አንዱ ሲሆን ዲዛይኑም የወደፊት ሶቬት ሕብረትን ፍላጎት ለማንፀባረቅ እንደሆነ ይወሳል። እንደ ክር የተጥለፈለፈው የዛሬው ሜትሮ ስራ ሲጀምር ‘ከሶኮልንኪ እስከ ፓርክ ኩልተሪ’ ጣቢያዎች የሚያካልል ቀይ መስመር ሲሆን ቀጥሎም ስሞሌንስካያ እስከ ኦክታኒ ሪያድ ባቡር ጣቢያዎች የሚሸፍን ሰማያዊ መስመር ነበር። እንደ ዕድል ሆኖ ካረፍኩበት ሆቴል እስከ ስልጠና ቦታዬ ለመድረስ ቀዩ መስመር ስለነበር የሜትሮ ጣቢያዎችን በቅጡ ለመጎብኘትና ለመደነቅ ችያለሁ። በርካቶቹ ቀደምት ጣቢያዎች ከዲዛይናቸው፣ ከታሪካቸው፣ ከቅርጻ ቅርሶች፣ ስዕላትና አጠቃላይ ስነ ውበት ሲታይ ‘የስርቻው ስር ቤተ መንግስት’ ብቻ ሳይሆን ቤተ መቅደስ የሚመስል ግርም ሞገስ አላቸው። እያንዳንዱ ጣቢያዎች የራሳቸው ልዩ አስደማሚ መልክና ማንነት አላቸው። ሜትሮ ግንባታው ጥልቀት ምስጢር የአፈሩ ሁኔታ እንደሆነ ይነገራል። በመስመር ቁፈራው ወቅትም በርካታ የከርሰ ምድር ወንዞች ተገኝተዋል። በርግጥም እንደ ጸበል የሚፈስ ውሃ ከአንድ ጣቢያ ላይ አይቻለሁ። ሜትሮን ለመጀመሪያ ጊዜ ለተመለከተ ዓይኑን መጠራጠሩ አይቀርም። ሜትሮ ውጫዊ ውበቱ ብቻም ሳይሆን ቴክኖሎጂካል ስርዓቱ አስደናቂ ነው። ከመካከላችን የተወሰኑት በተደጋጋሚ የመጥፋት ችግር አጋጥሟቸዋል። ምክንያቱም ሜትሮ ጣቢያዎች አንድ መውጫና መግቢያ ብቻ ሳይሆን እጅግ ውስብስብ የተሳሰሩ መንገዶችና አቅጣጫዎች አሉት። በተለይም አብዛኛው ጣቢያዎች ከሌሎች ጣቢያዎች ውስጥ ለውስጥ የተሳሰሩ በመሆኑ ነው። ይህን ለመለየት ሜትሮ ብዙ አማራጮች አሉት። ሜትሮ የተሰኘው የሞባይል አፕሊኬሸን (እንደ ጎግል ካርታ) ትልቁ መሳሪያ ነው። ከየት ተነስቶ የት መድረስ እንዳለበት ከነአጭር አማራጮች የሚናገር። በየትኛው በር መስመር መቀየር እንደሚገባ፣ መስመሩ ምን አይነት ቀለም እንዳለው ቁልጭ አድርጎ ያሳያል። በየፌርማታ ጣቢያዎች ላይም አቅጣጫ ጠቋሚ አማራጮች ያሉ ሲሆን ባቡሩ ውስጥ በራሱ በዲጂታል ስክሪን አመላካች አማራጮች አሉት። በዚህ ካልሆነ ግን ሜትሮ ከተማዋን በሶስት ቀለበት ይዞራታል። እያንዳንዱ ቀለበት ከሌላው እንደ ቀለበት በሁሉም አቅጣጫ እንደ ሸረሪት ድር የተሳሰሩ ነው። 397 ኪሎሜትር ርዝመት ያለው የሞስኮ ሜትሮ በስም፣ በቁጥርና በቀለም የሚለዩ 17 የሜትሮ መስመሮች፣ 265 የሜትሮ ጣቢያዎች(ፌርሜታዎች) አሉት። ወደ ሜትሮ ለመሳፈር እስከ 126 ሜትር የሚረዝሙ (740 ደረጃዎች) አሳንሰሮች (ኢሊቨተርስ) አሉት። የሞስኮ ሜትሮ በቀን እስክ 7 ሚሊዮን ሰዎችን እንደሚያጓጉዝ መረጃዎች ያሳያሉ። በነገራችን ላይ ሞስኮን ከሌሎች ከተሞችና ጎረቤት ሀገራት ጋር የሚያስተሳስሩ ባቡር ሌሎች ናቸው። ለነዚህ ፈጣን ባቡሮች ስምንት የባቡር ጣቢያዎች ሞስኮ ውስጥ ይገኛሉ። ሞስኮ ሜትሮ ከሌሊቱ 11፤30 እስከ ሌሊቱ 7 ሰዓት የሚያገለግል፣ በሰዓት 42 ኪሎሜትር የሚሸመጥጥ ነው። ለአንድ ጉዞ ትኬት 60 ሩብል (0 ነጥብ 6 ዶላር ገዳማ) ይከፈላል። ክፍያውን በራስ አገዝ ማሽኖች ወይም በስልክ መክፈል የሚቻል ሲሆን ለሜትሮና ለህዝብ ባስ ለሁለቱም የሚያገለግል አንድ ካርድ አለ። ያ ካርድ ያልያዘ ሰው ወደ ሜትሮ ለመግባት መሿለኪያ በሮች አይከፈቱለትም። በርግጥ ሞስኮ እንኳን ሜትሮ የትም ቦታ ገንዘብ ክፍያ በጥሬ ሳይሆን ገንዘብ በተሞላ ካርድ (ከባንክ ሂሳብ ተቆራጭ በሚያደርግ) በኩል ነው። ለሻይ ሂሳብም በካርድ መክፈል ይሻላል። ዲጂታላይዜሽን ማለት እንዲህ ነው። መውጫ ስለሞስኮ መተረክ ‘ዓባይን በጭልፋ’ ነው። ከተማው ጥልቅና ሰፊ ነው። ይህ የእኔ ቁንጽል ማስታወሻ ነው። አፍሪካዊያንን ያስደነቀን፣ በቁጭት ያነደደን ጉዞ ነበረን። ሞስኮ የሀገር ፍቅርና ኩራት፣ ብሔራዊ ትዕምርት ፈጠራን፣ የቴክኖሎጂና ፈጣራ ከፍታና ሚናን፣ በራስ ባህልና ታሪክ መኩራትን ታስተምራለች። የዲጂታላይዜሽን ደረጃና የሩስያ የኢንቮርሜሽን ኮሚዩኒኬሸን ቴክኖሎጂ ምጥቀት ያስገርማል። ይህ በቢሮክራሲና በሙስና የታጠረ ኅላቀር አሰራር ላይ የተቸከለውን የአፍሪካ ሀገራትን አሰራር ለማዘመን ትልቅ የቤት ስራ የሚሰጥ ነው። ብዝሐ-ማንነት ቀጣይነት ያለው ስልጣኔ፣ ዕድገትና ብልጽግና ለማረጋገጥ እንቅፋት አለመሆኑን አያሌ የብሔር ማንነቶችን ያቀፈችው ኢትዮጵያን መሰል በማንነት ተኮር ግጭት ሰለባ ለሆኑ ሀገራት ትልቅ ትምህርት ይሰጣል። ሀገር ዘላለማዊ ክብሯንና ሉዓላዊነቷን ለማስቀጠል በኢኮኖሚ መደርጀት፣ የጦር አቅሟን ማፈርጠም እና የሰው ሀብቷን በዕውቀትና ክህሎት ማልማት እንደሚገባት ከሩስያ በላይ ምሳሌ የለም። ሩስያ በራስ መልክ መዘመን፣ በራስ ጥበብ መራቀቅ፣ በራስ ፈጠራ የሰው ልጅን እንከን መቅረፍ እንደሚቻል በቋንቋቸው አሳይተዋል። በዓለም አቀፍ ስነ ፅሁፍ ምህዳር ውስጥ በመልማቱ የሚታወቀውና የራሱ ፊደል ያለው ሩስያኛ ቋንቋ ከቋንቋ ዕድገት ባሻገር ከቴክኖሎጂ ጋር እንዴት የተጣጣመበት ርቀት ያስቀናል። ኢትዮጵያን መሰል የራሳቸው ፊደል ያላቸው ሀገራት ቋንቋቸውን እንዴት ማልማት እንደሚችሉ ቁምነገር የሚያስጨብጥ ይመስለኛል።
በልጆቿ የጀግንነት ተጋድሎ ነፃነትን ሳትራብ ዘመናትን የተሻገረች-ኢትዮጵያ
Mar 1, 2023 7435
በቀደሰ ተክሌ (ሚዛን አማን ኢዜአ) ነፃነት የሰው ልጅ ከፈጣሪ ከተቸሩት ፀጋዎች አንዱና ዋነኛው ነው፤ በራስ ፈቃድ መወሰን፣ በራስ መሻት መከወንና በራስ ማንነት መኖር የሰው ልጅ የነፃነት አብነቶች ናቸው። ፈጣሪ ይህን ፀጋ የቸረው ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ ነው። ይሁን እንጂ ይህን ከፈጣሪ የተቸረውን ነፃነት በራሱ በወገኑ የመነጠቅ ዕጣ ፈንታ መግጠሙ አልቀረም፤ ነፃነቱን በራሱ ወገን እየተነጠቀ በራስ ፈቃድ መወሰን የማይችል እንዲሆን ተደረገ። ጥቁር ሕዝቦች በተለይም አፍሪካውያን በነጮች ዘንድ የባርነት ግብር ተሰጣቸው። ቅኝ መግዛት ለእነሱ የኃያልነት መገለጫ አድርገው መረጡ። በዚህም አፍሪካን ተቀራምተው የራሳቸው አደረጉ። ያኔ ቅኝ ግዛት አስተዳደር ዘመናቸው በራስ እምነት መቆም፣ በራስ ባህል፣ ወግና ማንነት መኖር አይታሰብም። የሰው ልጅ ከቆዳ ቀለም ልዩነት በስተቀር በራሱ አምሳል ለተፈጠረው ሰው ተገዥ ይሆን ዘንድ አውሮፓውያን ከእኛ ውጭ ሰው ብለው በግዞት የያዟቸውን አገሮች ዜጎች የስቃይና የመከራ ህይወት እንዲያሳልፉ ፈረዱ። ከባዱን የባርነት ቅንበር በጫንቃቸው ላይ ጫኑ። ማንነታቸውን አስረስተው ያሻቸውን አደረጉ። የቅኝ አገዛዝ ገፈት ቀማሽ እንድትሆን ፅዋ የደረሳት የጥቁሮች ፈርጥ ኢትዮጵያ ግን እንዲህ በቀላሉ ለቅኝ ገዥዎች እጅ አልሰጠችም። ሰውን በሰውነቱ ብቻ የምታከብረው ኢትዮጵያ የልጆቿ ነፃነት በማንም ቁጥጥር ስር እንዲወድቅ አልፈቀደችም።ኢትዮጵያን አፅንቶ ያቆማት በመከባበርና በአብሮነት ላይ የታነፀ ባህል፣ እሴት፣ ወግና ሥርዓት በባዕዳን እጅ ወድቆ ከሚከስም ''እኛ እንቅደም'' የሚል ጠንካራ የሀገር ፍቅርና ወኔ በአበራኮቿ ክፋይ ልብ ውስጥ እንደ አቶን እሳት ተንቀለቀለ። በፈጣሪያቸው እንጂ በምድራዊ ኃይል የሚመኩ አይደሉምና ቅኝ ሊገዛቸው የመጣን የውጭ ወራሪ ኃይል በጀግንነት ታግለው የኢትዮጵያን አንድነት፣ ነፃነትና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅና ለማስከበር በአንድ ልብ ወስነው ቀፎው እንደተነካበት ንብ ወደ አውደ ገባሩ ተመሙ። ኢትዮጵያዊ አንድነትን ኃይል፤ ወኔና ሞራልን ትጥቃቸው አድርገው በዓድዋ ተራራ እስከ አፍንጫው ዘመናዊ የጦር መሳሪያ የታጠቀውን የኢጣሊያ ጦር ገጠመ። ደረታቸውን ለጥይት ሰጥተው ተፋለሙ፣ ደማቸውን አፍሰው፣ አጥንታቸውን ከስክሰው ለእኛ ለልጆቻቸው ነፃነትን አወረሱ፤ ለምንምና ለማንም የማይበገረው ኢትዮጵያዊ አንድነትን ትጥቅና ስንቃቸው ያደረጉትን የኢትዮጵያውያንን ከብረት የጠነከረ ክንድ መቋቋም የተሳነው ወራሪ የኢጣሊያ ኃይል ገሚሱ የጎራዴ እራት ሲሆን፤ ቀሪው ቁስለኛና ምርኮኛ ሆነ፤ ሌላው ደግሞ እግሬ አውጣኝ ብሎ ህይወቱን ለማትረፍ እግሩ ወደመራው ፈረጠጠ። ጅግኖች አባቶቻችን ደማቸውን አፍሰው፣ አጠንታቸውን ከሰክሰው የኢትዮጵያ ክብርና ሉዓላዊነት አስጠብቀውና አስከብረው የፈጣሪ ልዩ ፀጋ የሆነውን "ነፃነት" ለዛሬው ትውልድ አስረከቡ። ኢትዮጵያም በትውልድ ቅበብሎሽ ሉዓላዊነቷምን አፅንታ የቆመች ነፃ አገር ሆና ቀጠለች። በዘመኑ የነበረውን ጥቁር ነጭን ማሸነፍ አይችልም የሚለውን አስተሳሰብ በሀገር ፍቅርና ወኔ ወራሪውን የፋሽሽት ኢጣሊያ ኃይል በጦር በጎራዴ አርበድብደው ድል በመንሳት ጥቁር ነጭን ማሸነፍ እንደሚች በቅኝ ገዥዎች የአገዛዝ አስተዳደር ስር ወድቀው ለነበሩ የዓለም ጭቁን ሕዝቦች በተግባር አረጋገጡ። በደማቸው ዘመን ተሻጋሪ ደማቅ የአርነት የታሪክ ድርሳን ጻፋ። በዘመን ጅረት የማይወይብ ታሪክ የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም በዓድዋ ተራሮች ላይ ተጻፈ። ኢትዮጵያ በልጆቿ አንድነትና የጀግንነት ተጋድሎ ነፃነት ሳትራብ ዘመናትን ተሻገረች። የነፃነት ዓርማ ሆና ለአፍሪካውያን ታየች። የዓድዋ ድል በቅኝ አገዛዝ አስተዳደር ስር ወድቀው ይሰቃዩ የነበሩ የዓለም ጭቁን ሕዝቦች በተለይም አፍሪካውያን የአርነት ትግል አድርገው የግፍ፣ የስቃይና የመከራ ቀንበርን ከጫንቃቸው ላይ አሽቀንጥረው እንዲጥሉ የፃነት ተምሳሌት ሆነ። በኢትዮጵያ የተለኮሰውን የነፃነት ችቦን አቀጣጥለው ብርቱ የአርነት ተጋድሎ አደረጉ፤ በዓድዋ ድል ከቅኝ ገዥዎች መዳፍ አፈተለኩ። የጥቁር ጭቁን ህዝቦች ነፃነት በዓድዋ የድል ገድል ለዓለም ታወጀ። አፍሪካውያን በራሳቸው ቋንቋ በነፃነት መናገር፣ በራሳቸው ባህል፣ወግና ሥርዓት እንዲሁም በራሳቸው መሪ ወደ ሚተዳደሩበት ምዕራፍ ተሸጋገሩ።የዓድዋ ድል ነገሮች አልጋ በአልጋ ሆነው በቀላሉ የተገኘ አይደለም። ኢትዮጵያውያውያ ለሀገራቸው ባላቸው ቀናሂነትና ከብረት በጠነከረ አንድነትና በጀግንነት ተጋድሎ ተጋምዶ በተደረገ እልህ አስጨራሽ ትግል እንጂ። የዓድዋ ድል ዛሬም ወደ ጀመርነው የልማት፣የዕድገትና የብልፅግና ማማ ላይ የሚያደርሰን መሰላል ነው። ይህ የሚሆነው ግን የአንድነት ኃይል ከጀግንነት ወኔ ሳይነጣጠል ፀንቶ ሲቆይ ብቻ መሆኑ እሙን ነው። ቀደምት አባቶቻቸን የዓድዋ ከፍታን በክብር መቆናጠጥ የቻሉት ዘር እየቆጠሩ ሳይሆን በኢትዮጵያዊ አብሮነትና አንድነት ተጋምደውና ተሰናስለው ነው። ያላቸውን የአንድነት ኃይል ተጠቅመው ድልን ተጎናጸፉ። በየዓመቱ ዓድዋን መዘከር ራስን ''እኔስ ምን ማድረግ እችላለሁ?'' በሚል እሳቤ ከሆነ ዓድዋ ህያው ነው፤ ወደ አለምነው የስኬትና የብልፅግና ከፍታ ላይ የአንድነታችን ኃይሉ እንደሚያደርሰን እሙን ነው። እንደ ቀደምት አባቶቻችን በተጋመደ ኅብረ ብሔራዊ አንድነታችንን በማጠናከር በኢኮኖሚው፣ ማኅበራዊ፣ በፖለቲካው ያሉ ፈተናዎችን በሀሳብ ልዕልና በማሸነፍ ለሌላ ድል መትጋት አለብን። አንድነታችንን በማፅናት በኅብረት ለኢትዮጵያ ከፍታ መትጋት ከሁላችንም ይጠበቃል።"ድር ቢያብር አንበሳ ያስር" እንዲ ሀገራዊ ብሂሉ ከተባበርን የማናልፈው ፈተና አይኖርም። አንዴ በጦርነት ሌላ ጊዜ በድርቅና በሌሎች መንስኤዎች ያጋጠሙንን ተግዳሮቶች በአብሮነት ተጋፍጠን ድል እያደረግን መጥተናል። ፈተና ሁሌም ይኖራል፤ ማሸነፍና መሸነፍ ግን በእኛ ፅናትና ጥንካሬ ይወሰናል። ለወደፊትም የሚያጋጥመንን ፈተና አንድነታችንን አፅንተን ኅብረታችን ለሀገራችን ልማት፣ ዕድገትና ብልፅግና በማዋል በርካታ ዓድዋዎችን እንሰራለን። የዓድዋ ድል ከኢትዮጵያ አልፎ ለመላው ጥቁር ጭቁን ህዝቦች የኩራት ምንጭ የነፃነት ዓርማ ነው። የዓድዋን ታሪክ መጠበቅና መደጋገም የእኛ የኢትዮጵያውን ኃላፊነትና ግዴታ ነው። ልዩነትን መስበክ ከኢትዮጵያዊ ከፍታ መሸራተት ነው። እኛነትን ረስቶ እኔ ማለት የዓድዋን ታሪክ መሸጥ ነው። ኢትዮጵያውያን አንድ ሆነን እንጂ ተከፋፍለን የሰራነው ታሪክ የለም። የትናንት መልካም ስምና ዝና ከዘመኑ ጋር አብሮ ከፍ ከፍ እያለ አብቦ ማፍራት እንጂ፤ በልዩነት አስተሳሰብና አመለካከት ሊኮሰምን አይገባም። የኢትዮጵያውያን የአንድነትና የሉዓላዊነት መገለጫ፣ የዓለም ጭቁን ሕዝቦች የነፃነት ተምሳሌ-ዓድዋ ለዘላለም በክብር ሲዘከር ይኖራል‼
ሽሬ ወአክሱም (የአልፎ ሂያጁ ማስታወሻ)
Jan 25, 2023 5996
ሽሬ ወአክሱም (የአልፎ ሂያጁ ማስታወሻ) አየለ ያረጋል (ኢዜአ) መዳረሻዬ ሽሬ እንዳስላሴ ነው። ለዘገባ ሥራ ከባህርዳር- ጎንደር- ደባርቅ- ሸሬ መንገድ ከሚዲያ ባልደረቦች ጋር እየተጓዝኩ ነው። የጥምቀት ሙሽራዋ ጎንደር እየተኳኳለች ነበር። ደባርቅ ከመድረሴ በፊት ዳባት ትገኛለች-የደጃች አያሌው ብሩ ቁርቁር ከተማ። ደጃች አያሌው ትውልዳቸው በጌምድር ጋይንት ቢሆንም ግዛታቸውና ኑሯቸው ዳባት ነበር። ሞገደኛው ደጃዝማች አያሌው ብሩ በጎንደር ማኅበረሰብ ዘንድ ዝናቸው የናኘ ነው። ደጃዝማች አያሌው በ20ኛው ክፍለ ዘመን መባቻ (ከልጅ ኢያሱ እስከ አጼ ኃይለሥላሴ ዘመነ-መንግሥት) ታሪካዊ ክንውኖች ጉልህ ተሳትፎ አላቸው። አንዷን ብቻ ልምዘዝ። ራስ ተፈሪ ‘ንጉሠ-ነገሥት አጼ ኃይለሥላሴ’ ደጃች አያሌው የቅርብ ዘመዳቸውን ራስ ጉግሳ ወሌ ብጡልን (የንግሥት ዘውዲቱን ባለቤት) ወግተው የጎንደር ግዛት ‘ራስ’ ተብለው ለመሾም ቃል ቢገባላቸውም፤ ተልዕኳቸውን ተወጥተው ቃሉ ባለመፈጸሙ ደጃዝማቹ ከአጼው ጋር መቀያየማቸው አልቀረም። በዚህም:- "አያሌው ሞኙ፣ ሰው አማኙ ሰው አማኙ፣ የአያል ጠመንጃ፣ ስሟን እንጃ ስሟን እንጃ…” በማለት የጎንደር አዝማሪ አዚሟል። ዛሬም ይህ ግጥም የብዙ ባህላዊ ዘፈኖች አዝማች ነው። ደጃች አያሌው ብሩ ደፋር ናቸው ይባላል። ከአጼ ኃይለሥላሴ ጋር ቢቀያየሙም በ1928 ዓ.ም ፋሺስት ኢጣሊያ ወረራ ሲመጣ ቅድሚያ ለአገሬ ብለዋል። ‘የተደበቀው ማስታወሻ’ በተሰኘው የዶክተር ሀራልድ ናይስተሮም (ትርጉም ገበየሁ ተፈሪ እና ደሳለኝ አለሙ) መጽሐፍ እንደተጠቀሰው ደጃች አያሌው “ንጉሡ እንደኛ ሰው ናቸው። ኢትዮጵያ ግን የሁላችንም ናት" ብለው ጦራቸውን መርተው በሽሬ ግንባር ዘምተዋል። ጉዟችን ቀጥሏል። ደባትን እያለፍን ነው። ‘እንኳን ደህና መጡ፤ ወደ ጭና ታሪካዊቷ ሥፍራ’ የምትለዋን ታፔላን በስተግራ እያየን ወደ ደባርቅ ገሰገስን። የሰሜን ተራሮች የብርድ ወጨፎ ያረሰረሳትን ደባርቅን ከማለፋችን ሊማሊሞ ጠመዝማዛ ቁልቁለት ተቀበለን። አስፈሪ የሊማሊሞ መልክዓ ምድር የደጋው ሰሜን ውርጭ እና የተከዜ በርሃ ኬላ ነው። ባለቅኔው ጸጋዬ ገብረመድህን “የሰማይ የምድሩ ኬላ፣ የየብስ የጠፈሩ ዋልታ አይበገር የዐለት ጣራ፣ አይመክተው መከታ ሊማ-ሊሞ አድማስ ሰበሩ፣ በጎማ ፈለግ ይፈታ? በትሬንታ እግር ይረታ?…” ብሎ የመኪና መንገድ ተገንብቶበት በማየቱ ግርምቱን የተቀኘለትም ለዚህ ይመስላል። ከሊማሊሞ ቁልቁለት በኋላ አዲ-አርቃይ፣ ዛሪማ፣ ማይፀብሪ እና ሌሎች የጠለምት ወረዳ ከተማዎችን አልፈን፤ የዋልድባ ረባዳማ አካባቢዎችን ተሻግረን ተከዜ ወንዝ ደረስን። የዚህን መንገድ እና ተከዜ ወንዝን ሳስብ የሀዲስ ዓለማየሁ ትዝታ አስተከዘኝ። የፋሺስት ኢጣሊያ ወራሪ ጦር የወገንን ጦር ፊት ለፊት መቋቋም ሲሳነው በሰው ልጆች ላይ ተደርጎ የማያውቅ መርዝ በጅምላ የፈጀበት አሳዛኝ ታሪክ ነበር። በተከዜ ወንዝ ውሃን በመመረዝ የወገን ጦር ያለቀበት ሥፍራ ነው። የተከዜ ሸለቆ በኢትዮጵያዊያን ደምና አጥንት ዋጋ የተከፈለበት ነው። ሀዲስ ዓለማየሁ በአንድ ዕለት የተመለከቱትን እንዲህ ጽፈውታል። “የተከዜ ውሀ እመሻገሪያው ላይ ሰፊና ፀጥ ያለ ነው። ታዲያ ያ ሰፊ ውሀ፤ ገና ከሩቅ ሲያዩት ቀይ ቀለም በከባዱ የተበጠበጠ ይመስላል። “ምን ነገር ነው፤ ምን ጉድ ነው?” እየተባባልን ቀረብ ስንል መሻገሪያው በቁሙም በወርዱም ከዳር እስከ ዳር ሬሳ ሞልቶበት የዚያ ሬሳ ደምና ፈርስ ነው። የሰው ሬሳ፣ የፈረስ እና የበቅሎ ሬሳ፣ ያህያ ሬሳ፣ ያውሬ ሬሳ፥ ሬሳ ብቻ! እግር ከራስ ራስ ከእግር እየተመሰቃቀለ እየተደራረበ ሞልቶበት፥ የዚያ ሁሉ ሬሳ ደምና ፈርስ ነው”። ይሉናል። ቀጥለውም “በእውነቱ እንዲህ ያለውን መሳሪያ ምንም ጠላት ቢሆን በሰው ላይ ለማዋል የሚጨክን ሰው፥ ሰብዓዊ ስሜት የሌለው፣ አለት ድንጋይ የተፈጠረበት መሆን አለበት፤ እንዲህ ያለውን መሳሪያ በሰው ላይ ማዋል ሰብዓዊ ህሊና ሊሸከመው የማይችል እጅግ ከባድ መሆኑን ዓለም ሁሉ ያወቀውና ያወገዘው በመሆኑ የኢጣሊያ መንግሥት በኢትዮጵያ ላይ ከማድረጉ በቀር “ሌላ መንግሥት በሌላ አገር ላይ አደረገ’ ሲባል ተሰምቶ የሚያውቅ አይመስለኝም” ብለዋል። ከተከዜ ባህር ማዶ ጉዞዬ ያገኘኋት ሌላዋ ታሪካዊ ሥፍራ እንዳባጉና ናት። እንዳባጉና የወገን ጦር ትልቅ ገድል የፈጸመበት ነው። ጀግኖች አባቶቻችን የጠላት ታንክ ሳያስፈራቸው የጠላት ጅምላ ጨራሽ ቦምብ ጣይ አውሮፕላን ተቋቁመው ጠላትን ድባቅ የመቱበት፤ ወደ አክሱም እንዲያፈገፍግ ያደረጉበት ሥፍራ ነው። “የጠላት ቦምብ ጣይ አውሮፕላን በጦር ሜዳው ትንንሽ ቦምቦች አውቶማቲክ ጠመንጃ ይተኩስ ነበር። አቢሲኒያኖች ደግሞ ከጠላት ጋር ግብግብ ገጥመው ጉዳይም አልሰጡትም ነበር…” ይላል ዶክተር ሀራልድ ‘የተደበቀው ማስታወሻ’ በተሰኘ መጽሐፉ። ይህ አካባቢ በሀገር ፍቅር የነደዱ ኢትዮጵያዊያን ደም ያፈሰሱበት፣ አጥንት የከሰከሱበት፤ ለኢትዮጵያ መስዕዋትነት የከፈሉበት ነው። ይህ የሀገርን ሉዓላዊነት ለማስከበር ዋጋ የተከፈለበት ቀጣና ነው። ቀኑ ተገባዷል። ጉዟችን እንደቀጠለ ነው። እኔም የማሽላ ማሳዎችን ግራ ቀኝ እየተመለከትኩ ለዕለቱ መዳረሻችን ወደሆነችው ሽሬ ከተማ ገባን። ሽሬ በትግርኛ ‘ሽረ’ ሲሉት ይደመጣሉ። በእርግጥ ሽሬን ለመጀመሪያ ጊዜ መርገጤ ነው። ዕለቱም ጥር ሥላሴ ነው። ሽሬ በጥር ሥላሴ ትደምቃለች፤ ሙሉ ስሟም ሽረ እንዳስላሴ ነው። የሽሬ ሥላሴ ጠበል ሽሬ ደርሰን ማረፊያችንን ያዝን። ጊዜው በጣም አልመሸምና ከተማዋን በቀላሉ መቃኘት ይቻላል። ሽሬ ሰፊና ደማቅ የዞን ከተማ ናት። ከመካከላችን የአንደኛው ባለሙያ ቤተሰቦች ሽሬ ነበሩና አስጠሩን። ለሥላሴ ጠበል ግብዣ። ባል እና ሚስቱ ከልክ በላይ መስተንግዶ አደረጉልን። ‘ጠብ እርግፍ አድርገው አስተናገዱን’ ማለት ይቀላል። እንግዳ መቀበል ነባር ኢትዮጵያዊ እሴታችን ቢሆንም ጦርነት ውስጥ ለቆየ አካባቢ የተለየ መልክ ነበረው። እንግዳ አቀባበላቸው በእርግጥም የመሃል አገር ሰው የናፈቃቸው ይመስላል። የተትረፈረፈ እህልና ውሃ አቅርበው በ’ብሉልን፤ ጠጡልን’ ተማጽኗቸው የተነፋፈቀ ቤተ-ዘመድ ግብዣ አስመሰሉት። የሥላሴው ጠበል የሸሬ ጠላ ቀረበ። የሸሬ ጠላ ሳስታውስ ፕሮፌሰር ሽብሩ ተድላ ታወሱኝ። የወቅቱ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምሀሩ ፕሮፌሰር ሽብሩ በዘመነ ደርግ በዕድገት በሕብረት ዘመቻ ተማሪዎቻቸውን ይዘው ሽሬ ዘምተው ነበር። በወቅቱ ታዲያ የሸሬ ጠላ ፍቅር ይዟቸው በየጊዜው ሲኮመኩሙ የተመለከቱ ሰዎች ‘ፕሮፌሰሩ ከጠፉ የሚገኙት ጠላ ቤት ነው’ ሲባሉ እንደነበር ‘ከጉሬ ማርያም እስከ አዲስ አበባ’ በተሰኘው ግለ ታሪካቸው አስፍረዋል። ከግብዣ መልስ ከማረፊያ ሆቴል ላይ ሆኜ ከተማዋን ስቃኛት ከጦርነት ድባቴ የተላቀቀች ይመስላል። የአመሻሽ ሕዝቡ እንቅስቃሴም ሆነ እስከ ሌሊቱ አጋማሽ የሚሰሙ የመዝናኛ ቤቶች ሙዚቃዎች የከተማዋን አሁናዊ መልክ የገለጠልኝ ነበር። ንጋት ላይ በቁርስና ቡና ሰዓታት ከሰዎች ጋር መስተጋብሬ ጀመረ። በጦርነት አዙሪት የከረመችው ሽሬና አካባቢው ኑሮ እጅጉን የከበደ ነበር። መልከ-ብዙ ማህበራዊ ቀውሶች አስተናግደዋል። አሁናዊ ምላሻቸው “ተመስገን፤ ያ ሁሉ አለፈ” የሚል ነው። ገበያው ተረጋግቷል፤ ማህበራዊ ኑሮ ተመልሷል። ድህረ-ሰላም ስምምነት ለሽሬ ነዋሪዎች ሁለንተናዊ እፎይታን አንብሯል። ከቀናት በኋላ በአክሱም የታዘብኩትም እንዲህ ነው። ኑሮን ያቀለለው የተቋማት አገልግሎት ጅማሮ በመጀመሪያ ዘገባ ስራዬ መሰረተ ልማትን አገልግሎት ቃኘሁ። ባንክ፣ ቴሌ፣ ሆስፒታል… መሰሎቹን። ተጠቃሚዎችንም፣ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት ስራ ሃላፊዎችንም አነጋገርሁ። ከሰላም ስምምነቱ ማግስት ጀመሮ ተቋማቱ ወደስራ መመለሳቸው ከሁለንተናዊ ችግር እንደታደጋቸው ያነሳሉ። በትራንስፖርት እየተንቀሳቀሱ፣ በኤሌክተሪክ ስራዎቻቸውን እየከወኑ ነው። ለሁለት ዓመታት የተቋረጠው አገልግሎት አቅርቦት እና የአገልግሎት ፈላጊዎች ፍላጎት ግን አሁንም ሙሉ በሙሉ ተመጣጣኝ እንዳልሆነ የተጠቃሚዎችም፤ የአገልግሎት ሰጭዎችም ሀሳብ ነው። በሽሬ ስሁል ሆስፒታል የተመለከትኳቸው፤ ያነጋገርኳቸው፤ ከታዳጊዎች እስከ አዛውንት ዕድሜ ያሉ ህሙማን የሰላም አየር ማግኘታቸው የሕይወታቸው ዑደት እንዲቀጥል አድርጓል። ድንገተኛም ሆነ ነባር ህመም ያለባቸው ሰዎች በነጻ እየታከሙ ነው ያገኘኋቸው። ሰላም ከሌለ መታከም ቀርቶ በቅጡ ማስታመም፤ በወጉ መቀበርም እንደማይቻል ገልጸውልናል። የጤና፣ የባንክና የቴሌኮም አገልግሎት የግብዓት ክፍተቶች የማሟላት ሰራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም በፌዴራል ደረጃ በየተቋማቱ የተመደቡ አስተባባሪዎች አረጋግጠውልኛል። የጸጥታ አካሉና የህብረተሰቡ ትብብርም የሚያስቀና እንደሆነ ግለሰቦችም፤ የጸጥታ አካላትም ነግረውኛል። አክሱም ጺዮን ማርያም፣ ሽሬ ስላሴ ንግስ፣ የጥምቀት በዓላት ከሶስት ዓመታት በኋላ በአደባባይ ታቦት ወጥቶ ተከብሯል። የፌዴራል ፖሊስ ተወካዮችም ይህንኑ ነው ያረጋገጡልኝ። የመከላከያ ሰራዊት አባላት ከከተማ ነዋሪዎች ጋር ያላቸው ግንኙነት ቤተሰባዊ የሆኑ ይመስላል። እንቅስቃሴያቸውም የሰላማዊ ቀጠና መልክ ያለው ነው፤ ዩኒፎርም ከመልበሳቸው በስተቀር ጀሌያቸውን ይንቀሳቀሳሉ። ይህ ደግሞ መተማመን ከመፍጠር ባለፈ ጦርነት ውስጥ ለቆየ ማህበረሰብ ከስነ ልቦና ጫና እንዲላቀቅ አይነተኛ ሚና እንደላው ይሰማኛል። ኢ-መደበኛ የሽሬና አክሱም ወጎች ያረፍኩበት ሆቴል ባለቤት ‘አደይ’ ተግባቢ ናቸው። ደግ እናት ይመስላሉ። ከገባን ጀምሮ ‘ጠላ ተጎንጩ፤ ቡና ጠጡ’ ጭንቃቸው ነው። ሁለት ቀን ቡና አስፈልተውልናል፤ ጠላ አቅርበው ዘክረውናል። ይህ ሁሉ ሲሆንም ለከተማው እንግዳ መሆናችንን እንጂ ስለሙያችንም ሆነ ስለሌላ ማንነታችን አያውቁም ነበር። ብዙ መጨዋወትና ውሎ አዳር በኋላ ነው ጋዜጠኛ ስለመሆናችን ያወቁት። አደይ ተጨዋች ናቸው። አማርኛ ያዝ ቢያደርጋቸውም ጨዋታቸው ‘ኩርሽም’ ነው- ተሰምቶ የማይሰለች። በአጋጣሚ ‘ሰለክላካ’ ስለምትባለዋ ታሪካዊ ሥፍራ ጠይቄያቸው እያወጋን ነበር። ‘እንደእናንተ ወጣቶች ሳለን ‘ሰለክላካን ያላዬ ሸዋን ያመሰግናል’ ይባል ነበር። ታዲያ አንድ የሸዋ ሰው መጣና ሰለክላካን አየና ‘በቃ ይቺ ናት’ ሰለክላካ’ ብሎ ተገረመ” ብለው አሳቁን። (የፍቅር እስከ መቃብር መሪ ገጸ-ባህሪው ‘በዛብህ’ ወደ ዲማ ጊዮርጊስ ሄዶ ‘የዲማ መልኳ እና ዝናዋ’ ተጣርሶበት እንደተገረመበት ቅጽበት መሆኑ ነው)። አደይ የተጀመረው ሰላም ፍጹም ምሉዕ ሆኖ ወደ ቀደመ ኢትዮጵያዊ መልካችን የምንመለስበት ጊዜ እንዲመጣ ይሻሉ። ከጦር-ነት ወደ ሰላም-ነት! ቆንጂዬዋ ፊዮሪ የኮሌጅ ተማሪ ነበረች። በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅት ጀምሮ በኋላም በጦርነት ሳቢያ ትምህርቷን ካቆመች ሦስት ዓመታት ሆኗታል። ጦርነቱ ከቆመ በኋላ የጀበና ቡና ጀምራለች። ደንበኞቿ ሰብሰብ ብለን እንቀመጣለን። ፊዮሪ ከስኒ ማቅረቢያዋ ላይ አነስተኛ ጀበናዋን፤ የሚያማምሩ ስኒዎቿን እና መዓዛው ከሚያውድ የዕጣን ማጨሻዋ ጋር ሰድራ ይዛ ትቀርባለች። ከመካከላችን ካለው ጠረጴዛ ላይ ታስቀምጥና እርሷም ወንበር ይዛ ከመካከላችን ትቀመጣለች። ቡናው እስኪሰክን ጨዋታዋን ታስኮመኩመናለች። ቡናው ከሰከነ በኋላ ቡናዋን ቀድታ ለእያንዳንዳችን በእጃችን እያነሳች ትሰጣለች። በሽሬ ቡና የሚቀርበው በዚህ መልክ ነው። ለፊዮሪ እና መሰሎቿ ጦርነቱ ክፉ ጠባሳ መጣሉ፤ ተስፋቸው ላይ መጥፎ አሻራ ማስቀመጡን ታነሳለች። አሁን ግን ብሩህ ተስፋ ሰንቃለች። ስለነገዋም “ሰላሙ ይዝለቅልን፤ ትምህርቴን ለመቀጠል እመኛለሁ” ትላለች። አክሱም ከሽሬ በስተሰሜን 60 ኪሎ ሜትር ይርቃል። ከሽሬ አክሱም ስንንቀሳቀስ ከጥምቀት ዕለት በስተቀር ገበሬው የግብርና ሥራዎቹን እየከወነ ነበር። አርሶ አደሩ ያርሳል፤ መስኖውን ያለማል። የተዘራውን ውሃ ያጠጣል። የበቀለ ቡቃያውን ይኮተኩታል። ከጦርነት ወደ ልማት መዞሩን ዐይኔ ታዝቧል። በጥምቀት ዋዜማ፤ የከተራ በዓል ዕለት ሁለት ጎራማይሌ የረፋድ ትዕይንቶችን ላንሳ። ከአክሱም ከተማ ወደ አድዋ እና ሽሬ መገንጠያ አካባቢ ሰፊ የቀንድ ከብት ገበያ ነበር። እውነተኛ የዓመት በዓል ገበያ መልክ ያለው ትዕይንት ነበር። በተለይም የፍየል ዋጋ በተመጣጣኝ ዋጋ እየተገበያዩ እንደነበር ሰምቻለሁ። ታሪካዊቷን አክሱም ከተማ ለመጨረሻ ጊዜ የረገጥኳት/የተሳለምኳት ከአራት ዓመት በፊት በ2011 ዓ.ም ይመስለኛል። ከገበያው ቀጥሎ በታቦተ-ጽዮን መገኛዋ ርዕሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ደጅ፣ በጥንታዊያኑ የአክሱም ሐውልት መገኛ አደባባይ ነበር። ከጽዮን በስተምዕራብ በአርባቱ እንሰሳ በኩል፤ በቅዱስ ያሬድ ዋርካ… አድርጌ በጽዮን ዋናው በር ደረስኩ። ማራኪ የአክሱም የኮብልስቶን መንገዶች ኦና ናቸው። የወትሮው ግርግር ናፍቋቸዋል። ከጽዮን ቅጥር ግቢ በዋናው በር በስተውጭ አነስተኛ እና ብቸኛ ዋንዛ በኮብልስቶን መሃል ነበረች። ዛሬም ለምልማ አለች። በዚህ አካባቢ ድሮ የነጭ ጎብኚ ጋጋታ፣ የጽዮን ደጅ ጠኚ ምዕመን… የተጨናነቀ ነበር። እንደ ድሮው የፎቶ አንሺ ግርግር፣ የአክሱም መስቀል ቀርጸው የሚሸጡ ወጣቶች ጫጫታ የለም። ይልቁንም እርጥባን የሚሹ አቅመ ደካሞችና ህፃናት ነበሩ። ጦርነት የሥፍራዋን መልክ አጠይሞታል። ያም ሆኖ ከተማዋ የንግድ እንቅስቃሴ ሙሉ በኩሉሄ ባይባልም ወደነበረበት እየተመለሰ ነው። የግልም ሆነ የመንግሥት ባንኰች ሥራ ከጀመሩ ሰነባብተዋል። ከአክሱም ሐውልት ወደ ሌላ ሰፈር አቀናሁ። ትርሐስ ገና ታዳጊ ልጅ ነች። ጠይም፤ ስርጉድ፣ ሳቂታና ተረበኛ አይነት ልጅ ነች። እንደ ሽሬዋ ፊዮሪ መንገድ ዳር የጀበና ቡና እየሰራች ነው። ከሩቅ የመጣን እንግዶች መሆናችንን ስታውቅ፤ ደስታዋ ከገጿ ይነበብ ነበር። ያለፉ ጊዜያትን ሰቆቃ አጫወተችን። ስለቀጣይ ዕጣ ፈንታዋ እና ዕቅዷ ስታወራ ትቆይና “የሰው ልጅ ግን በጣም ከሃዲ ነው። ከወራት በፊትኮ ስለቢዝነስ አላስብም ነበር። መቼ እሞታለሁ እንጂ” ብላ ራሷን ትወቅሳለች። ወደ ሰማይ አንጋጣ ፈጣሪዋን ታመሰግናለች። ጦርነት ተራውንም ሕዝብ ለመልከ-ብዙ ቀውስ ዳርጎት እንደቆየ ታነሳለች። ዛሬ ሁሉ አልፎ ሰላም መውረዱ ለመጨዋወት መብቃቷ ለእርሷ ትልቅ ብሥራት ነው። ይህ ለትርሐስ ብቻ ሳይሆን ለመላው አክሱማዊያን መሆኑ እሙን ነው። አክሱም ከተማ በመከላከያ ሠራዊት ቁጥጥር ሥር ከዋለችበት ጊዜ ጀምሮ በከተማዋ በሻለቃ አዛዥነት የተሰማራ የፌደራል ፖሊስ አባልም ያጋጠመውን አሳዛኝ ገጠመኞች አጫውቶኛል። ጦርነቱ ቢራዘም ኖሮ በተራው ሕዝብ ላይ ምን ያህል የከፋ ጉዳት ይደርስ እንደነበር በአሳዛኝ ሁኔታ ገልጾልኛል። አክሱሞች ያን ሁሉ አልፈው ሰላም አየር ነፍሶ፣ ከስጋት ቆፈን ተላቀው ወደ መደበኛ እንቅስቃሴ ተመልሰዋል። የዛሬ ሳምንት ሰርክ(11 ሰዓት) ላይ አክሱም የከተራ በዓል በድምቀት አክብራለች። ታቦተ-ጽዮን ወደ ባህረ- ጥምቀቱ ስትወርድ፤ ወግና ሥርዓቱ ተጠብቆ፣ ሕዝቡ በሀበሻ ነጫጭ አልባሳት፣ ካህናት በልብሰ ተክህኖ ደምቀው … እየተከወነ ነበር። አንዲት እናት ለአማርኛ ተናጋሪ በቀረበ አነጋገር እያለቀሱ ታቦት እየሸኙ ነው። ትኩር ብዬ ሳያቸውም ዕንባቸው ዱብ ዱብ ይላል። “ከዚያ ሁሉ መከራ አልፎ ለዚህ በቃን፤ ተመስገን” እያሉ እልልታውን ያቀልጡታል። በደስታ እያነቡ ነበር። ይህ ስሜት የብዙኃኑ አክሱማዊያን እናቶች እንደሆነ መገመት ቀላል ነው። አክሱም በኮቪድ እና በኋላም በጦርነቱ ምክንያት ባህረ-ምቀት ታቦት ወጥቶ ሲከበር ለመጀመሪያ ጊዜ ነበር። ከወትሮው በተለየ ድምቀትና ውበት በሰላምና በደስታ፤ በአደባባይ እልልታና ሆታ በማክበራቸው ልዩ ስሜት ፈጥሮባቸዋልና! እናም በአክሱም የከተራ ሆነ የበዓለ-ጥምቀት ክብረ-በዓላት በሰላም ስምምነቱ ማግስት በድምቀት ተከውኖ አለፈ። የሃይማኖት አባቶቹም ሆኑ ምዕመኑ በሰጡት ቃለ መጠይቅም የዘንድሮው ክብረ-በዓል ካለፉት ዓመታት ነባራዊ ሁኔታ ጋር እያነጻጸሩ፤ ትልቅ ብሥራትና መልክ እንዳለው ገልጸዋል። ሰላም እንዲጸና፤ ነባር ኢትዮጵያዊ አንድነትና መተባበር እንዲመለስ ጽኑ መሻታቸውን ነግረውናል። በበጎ ቀን የማውቃትን አክሱም፤ ከረዥም ጊዜ በኋላ አሁናዊ መልኳን ታዝቤ፤ የነገ ትዝታ ሰንቄ ተመለስኩ!! ሰላም ለኢትዮጵያ!!
ገና እና ላሊበላ
Jan 5, 2023 548
(ብርሃኑ አለማየሁ) በኢትዮጵያ በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ በድምቀት ከሚከበሩ ሃይማኖታዊ በዓላት መካከል የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል ወይም ገና አንዱ ነው። በዓሉ በሃይማኖት ተቋማቱ ሃይማኖታዊ ስርዓትና ትውፊት መሰረት ይከበራል። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን ከበዓሉ ዋዜማ ጀምሮ በሚከናወኑ የዝማሬና የመንፈሳዊ የጸሎት መርሐ ግብሮች አማካኝነት በዓሉ በልዩ ሁኔታ ይከበራል። የገና በዓል በቤተክርስትያኗ ስርዓትና ትውፊት በተለየ ሁኔታ ከሚከበርባቸው ስፍራዎች ቀዳሚው በሰሜን ወሎ ዞን አገረ ስብከት ስር የሚገኘው የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያን ነው። የላሊበላ አካባቢ የመሬት አቀማመጡ ለግብርና ባይጋብዝም፤ ፍሬያማነቱ በታላላቆች የጥበብ ንቃት የሚለካና ምርታማነቱም ባኖሩት የኪነ-ህንጻ ርቀት የሚመነዘር እንዲሆን አድርጎታል። ጥልቅ የኪነ ህንጻ ጥበብ ያረፈባቸው ዘመን ተሻጋሪዎቹ የላሊበላ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናት ፤ የቆየውን ሀይማኖታዊ ህይወትና ክንዋኔ ፈጣን በሆነው የዓለም ለውጥ ሳይበረዝ እንዲቀጥል ጠባቂ በመሆንም ወደር አይገኝላቸውም ፡፡ ቅዱስ ላሊበላ /ከ1180-1207 ዓ.ም/ ከአባቱ ጃን ስዩም እና ከእናቱ ኪርወርና ይባላሉ። በተወለደም ጊዜ በንብ ስለ ተከበበ እናቱ ማር ይበላል ለማለት "ላል ይበላል" ብላለች። በአገውኛ “ላል” ማር ማለት ነው። ከዚህ የተነሳ ስሙ “ላልይበላ” ተባለ። ቀደም ሲል ሮሀ በአሁኑ አጠራር ላሊበላ በመባል የሚታወቀው ቦታም ስያሜውን ያገኘው እንደ እ.ኤ.አ ከ1181-1221 ነግሶ ከነበረው የመጀመሪያው የዛግዌ ስርወ - መንግስት ንጉስ ላሊበላ መሆኑ ይነገራል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ስርዓት መሰረት የቅድስና ማዕረግ ከተሰጣቸው ነገሥታት መካከል አጼ ላሊበላ አንዱ ሲሆን፤ የተወለደበት ዕለት ታህሳስ 29 መሆኑን ገድሉ ይገልጻል። በዚህም የኢየሱስ ክርስቶስ እና የቅዱስ ላልይበላ የልደት በዓል በላልይበላ በጥምረት ይከባራል። የበዓሉ በጥምረት መከበርን አስመልከቶ ከታህሳስ 28 ከምሽት 2 ሰዓት ጀምሮ የሚካሄደው ሰርዓተ ማኅሌትና ዝማሬ ከዓለት ወደታች በሰው እጅ የተፈለፈሉትን አብያተ ክርስትያናት በተመስጦና በአድናቆት ለሚመለከተው ጎብኚ ሌላ ማራኪ ትዕይንት ይሆንበታል። በዓሉ ከላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዱ በሆነው ቤተ መድኃኔዓለም የሚከበር ሲሆን፤ የቤተ ክርስቲያን መረጃዎች በተባለው መጽሐፍ እንደተገለጸው ይህ ቤተ መቅደስ ቅዱስ ላሊበላ በሮሐ ከዓለት ከፈለፈላቸው አብያተ ክርስቲያናት አንዱ ነው። በዓሉም በዚህ ቤተ መቅደስ በአካባቢው ካሉ አብያተ ክርስቲያናት ከተውጣጡ ከ500 በላይ አገልጋዮች ህብረ ዝማሬ ማህሌት (ምስጋና) የሚታሰብ ይሆናል። አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ታሪክ መጽሐፋቸውና በዓሉን አስመልክቶ ከታተመው ሐመር መጽሔት እንደተመለከተው የገና በዓል አከባበር የሚጀምረው ከታህሳስ 23 (በዓለ ጊዮርጊስ) አንስቶ ሲሆን፤ እስከ ታህሳስ 29 ድረስ ይቀጥላል። የማኅሌቱን ስነ ስርዓት ስንመለከት አንድ ጊዜ 12 ገደማ ጥንግ ድርብ የለበሱ በአንድ በኩል ደግሞ ጥቁር ካባ የለበሱ ማኅሌታውያን እያሸበሸቡ ስርዓተ ማኅሌቱን ያከናውኑታል። ማዕጠንት የያዙ 4 ካህናትና ከ8 ያላነሱ ዲያቆናት ወርቅ ካባ ለብሰው፣ የወርቅ አክሊል ደፍተው፣ የወርቅ መስቀል ይዘው መለከት እየነፉ ዙሪያውን በመዞር ማህሌቱን ያጅቡታል። ይህ ታህሳስ 28 ከምሽቱ 2 ሰዓት ጀመሮ የሚከናወነው የማኅሌት ሰርዓት ሌሊት 10 ሰዓት ላይ በሰርዓተ ቅዳሴ ይተካና ታህሳስ 29 ቀን ከ12 ሰዓት ጀምሮ ደግሞ ከ11ዱ የላልይበላ ቤተ መቅደስ የተውጣጡ ሊቃውንት የበዓሉን ያሬዳዊ ዜማ ለማጀብ ወደ ማሜ ጋራ /ቤዛ ኩሉ ዓለም ሥነ ሥርዓት የሚካሄድበት ቦታ/ ይወጣሉ። ልክ አንድ ሰዓት ሲሆን፤ ከላይና ከታች የሚሰለፉ ካህናት ቦታቸውን ይይዙና እስከ 4 ሰዓት በሚፈጅ ክንውን እየተቀባበሉ ቤዛ ኩሉ ዓለም ዮም ተወልደ' የዓለም መድሃኒት ዛሩ ተወለደ የተባለውን ወረብ ያቀርባሉ። የበዓሉን አከባበር በላሊበላ ልዩ የሚያደርገው አንዱ ይህ “ቤዛ ኩሉ ዓለም" የሚባለው የቀለም ዓይነት ሲሆን፤ በወረቡ ትርጓሜ መሰረት ዝማሬው ለአገር፣ ለወገን፣ ለምድር ሰላም በረከት የሚጸለይበት ነው። ከትርክቱም በላይ ዛሬም ድረስ ተአምራዊ ጥበባቸው ያልተፈታው የላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት ዓለምን ማስደመማቸው እንደቀጠለ ፤ ታላቅነታቸው እንደቀደመ፤ ቅድስናቸው እንደጸናና የበርካታ ሰዎችን የመንፈስ ቀልብ እንደገዙ ከሚታሰበውም በላይ ልቀው የዘለቁ ናቸው። የገናን በዓል በላሊበላ ለመታደም እንዲሁም አብያተ ክርስቲያናቱንና መንፈሳዊ የበዓል ሥርዐቱን ለመጎብኘት የሃይማኖቱ ተከታዮችና በርካታ አገር ውስጥና የውጭ አገር ጎብኚዎች ወደ ላሊበላ ያቀናሉ። ላሊበላ ከተማ አብዛኛውን የኢኮኖሚ ምንጯንና ማህበራዊ መስተጋብሯን መሰረት ያደረገቸው ከላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ጎብኚዎችና እሱን ተከትሎ ባሉ የማህበራዊ ትስስር ጉዳዮች ነው ቢባል ማጋነን አየሆንም። በርካታ ጎብኚዎችም የአብያተ ክርስቲያናቱን የኪነ ህንጻ ልህቀት ከሀይማኖታዊ ክንዋኔው ጋር ለማጣጣም ገናንን ተከትሎ የሚመጣውን የጥምቀት በዓል ተመራጭ ያደርጋሉ፡፡ በዓላትን ተከትለው በሚቆሙት ገበያዎቹ ፤ ከመቶ ዓመታት በላይ እንዳስቆጠሩ በሚነገርላቸው ልዩ ባለአንድ ፎቅ መኖሪያ ቤቶች በአካባቢው ነዋሪዎች አጠራር “ህድሞ” በሚባሉት ሳይቀር መስህብነቱን ከፍ ያደረገ ነው፡፡ በዓሉን ለመታደምና ስለታቸውን ለመፈጸም የሚመጡ እንግዶች ላሊበላ የምትጠቀምበት መንገድም ሌላኛው አስደናቂ መስህብ ነው። የገና በዓል ከመከበሩ ሳምንታት በፊት አስቀድመው ወደ ላሊበላ የሚመጡ ሰዎችን እግር በማጠብ፣ ቤት ያፈራውን በማቅረብ ለዘመናት ያካበተ እሴት በአደባባይ ይገለጣል። በስፍራው ከሚገኙ ሁቴሎች ጀምሮ ቅርጻ ቅርጽ ሻጮችና ሌሎች ዘርፎች በገና ወቅት ገበያ የገበያ አድማሳቸው የሚሰፋ ይሆናል። ነዋሪውም ቢሆን በወደደው የእጅ ጥበብ የተካነ ፤ ከአባቶቹ በወረሰው ጥንታዊ የብራና ላይ ጽሁፎቹና ስዕሎቹ የደመቀና ከዘመናት በፊት ከጥበበኞቹ የወረሰውን ጥበብ በስጦታዎቹ ላይ የራሱን አሻራ ጨምሮ ይታያል፡፡ በላሊበላ በገና ሰሞን ከሚታዩ አስደናቂ ሁኔታዎች መካከል ተጠቃሽ የሚሆነው ደግሞ በዓሉን አስታኮ የሚከናወነው የሰርግ ስነ ስርዓት ነው። የላሊበላ ጎብኚና ተሳላሚ እድምተኛ የሚሆንበት ሰርግ። በሰርግ ስነ ስርዓቱ ቤተ ዘመድ ተሰባስቦ ፍቅርን የሚለዋወጥበት፣ ስለ ማህበራዊ ጉዳዮች የሚመክርበት ብሉልኝ ጠጡልኝ የሚልበት የላሊበላን እንግዳ በፍቅር ማዕድ የሚያስቀድስበትም ነው። ይህም የገና በዓል በላሊበላ ሃይማኖታዊ፣ መንፈሳዊ፣ ትውፊታዊ፣ ባህላዊ፣ ኢኮኖሚያዊና አገራዊ ፋይዳ እንዳለው የሚያመለክት ነው። ዓለምን በአንድ የሚያናግሩት ቅርሶች መገኛ የሆነው ላሊበላ ለነዋሪውም፡ ለመላው ህዝብም ለጎብኚዎችም ተመችቶ እያስደመመ እንዲቀጥል ቅርሶቹን መጠበቅና የአካባቢውን መሰረተ ልማት ማሟላት ያሻል፡፡
ቻይናን ሳስባት
Dec 22, 2022 299
(በረከት ሲሳይ) አፈሩን ያቅልልላቸውና በቅርቡ በሞት የተለዩን አምባሳደር እምሩ ዘለቀ ከዓመታት በፊት በአንድ የሬዲዮ ፕሮግራም ላይ ቀርበው በ1960ዎቹ ወደ ቻይና በማምራት፤ ሆንግ ኮንግን ጨምሮ የተለያዩ የቻይና ከተማዎችን ተዘዋውረው መመልከታቸውን በመግለጽ፤ በዚያን ጊዜ ቻይና የነበረችበትን የድህነት ሁኔታና አሁን ላይ የደረሰችበትን የዕድገት ደረጃ በማነጻጸር የነበራቸው አድናቆትና ግርምት አሁንም ይታወሰኛል። አለፍ ብለውም ቻይና ከ1970ዎቹ ጀምሮ ባልተቋረጠ የዕድገት ምህዋር ውስጥ በመግባት ከፍተኛ ዕድገት ያስመዘገበችበትን ሂደት ከኢትዮጵያ ጋር በትይዩ በማነጻጸር “እኛን ምን ነክቶን ነው?” በማለት አምባሳደሩ በቁጭት ያነሱት ጥያቄ ከዓመታት በኋላ ዛሬ ላይ እኔ በድጋሚ ላነሳው እወዳለሁ። ለአምስት ወራት ገደማ ለሙያ ሥልጠና በከረምኩባት የሩቅ ምስራቋ “ቻይና” በእውነቱ! ዕድገቷን አይቶ “እኛስ መቼ ነው እንዲህ የምንሆነው?” ብሎ አለማሰብ ከቶ አይቻልም። በዚህ ተጠየቅ፤ በቻይና በሄድኩባቸውና በደረስኩባቸው ከተሞች እንዲሁም በጎበኘኋቸው ተቋማት ሁሉ በዓይነ-ህሊናዬ ኢትዮጵያን እያሰብኩኝ ቆይታዬን አገባድጄ በቅርቡ ወደ አገሬ ተመልሻለሁ። ወረርሽኙና ቆይታዬ በቻይና የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ሥር በሚንቀሳቀሰው የቻይና ዓለም አቀፍ የፕሬስ ማዕከል ጋባዥነት ነበር ለአራት ወር ተኩል የሥልጠና ቆይታ ወደ ቻይና ያመራሁት። ሥልጠናው እኔን ጨምሮ ከ60 በማደግ ላይ ያሉ አገራት የተውጣጡ 75 ጋዜጠኞችን ተሳታፊ ያደረገ ነበር። ከኮቪድ ወረርሽኝ ጋር በተያያዘ ለበርካታ ተጓዞች ወደ ቻይና መግባት ከባድ በሆነበት ወቅት ሥልጠናው መካሄዱ አንዳንድ ሁኔታዎችን እንድጋፈጥ አስገድዶኛል። ቻይና ከመግባቴ በፊት በአዲስ አበባ ለአምስት ቀናት እንዲሁም ቻይና ከደረስኩ በኋላ ሥልጠናው በዋነኝነት ወደሚካሄድባት የቻይናዋ ርዕሰ ከተማ ቤጂንግ ከማቅናቴ በፊት ደግሞ በደቡባዊ ቻይና በምትገኘው ጓንዙ ከተማ ለአሥር ቀናት በድምሩ ለ15 ቀናት ተከታታይነት ያለው የኮሮና ምርመራ በማድረግ ወሽባ (ኳራንቲን) ውስጥ ማሳለፌ ከገጠሙኝ አስቸጋሪ ሁኔታዎች አንደኛው ነው። ምንም እንኳን ከኮቪድ ነፃ መሆኔ ተረጋግጦ ወደ ቤጂንግ ባቀናም አገሪቱ ወረርሽኙን ለመከላከል ያወጣችውን ፖለሲ ተከትሎ ሥልጠናውን አጠናቅቄ እስከምመለስበት ጊዜ ድረስ በየሁለት ቀናት የኮሮና ቫይረስ ምርመራ ለማድረግ መገደዴም ሌላው የገጠመኝ ፈተና ነበር። ቻይና ከመግባቴ አስቀድሞ በተለይም ስለ ወረርሽኙ ሁኔታና ቁጥጥር በተመለከተ ከነበረኝ ግንዛቤ በተጨማሪ ከሚመለከታቸው አካላት ገለጻ ቢደረግልኝም፤ በመጀመሪያዎቹ ቀናት መደናገር አልቀረልኝም። ነገሮች አዲስ ሆነውብኛል፤ በየሁለት ቀናቱ የኮሮና ቫይረስ ምርመራ በመደበኛነት ማድረግ፣ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ (ማስክ) ማድረግ፤ ወደየትኛውም የሕዝብ መገልገያ ሥፍራ ማለትም መዝናኛ ቦታዎች፣ ሱፐር ማርኬትና ሌሎች ሥፍራዎች ለመገኘት በእጅ ስልክ ላይ ባለው መተግበሪያ (ቢጂንክ ሄልዝ ኪት) አማካኝነት የምርመራ ውጤት በር ላይ ላሉ አሳላፊዎች ማሳየት በግዴታነት መቀመጡ ከነበረኝ ልምድ ጋር ፍጹም የተለየ ነው። ነፃ የምርመራ ውጤትን ሳያሳዩ የትም መግባትም ሆነ መንቀሳቀስ አይታሰብም። ጎን ለጎንም በርካታ ለወረርሽኙ አጋላጭ ናቸው የተባሉ የሕዝብ መሰብሰቢያ ሥፍራዎች ዝግ ናቸው፤ መዝናኛ ቦታዎችና የሕዝብ መገልገያ ማዕከላት ከመደበኛው ታዳሚዎቻቸው በእጅጉ አነስተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎችን ብቻ እንዲያስተናግዱ ተገደዋል፤ በአገሪቱ የሚካሄዱት እንቅስቃሴዎች ላይም እገዳ ተጥሏል። ኢትዮጵያን ጨምሮ ከሌሎች አገራት ወደ ቻይና የሚጓዙ የንግድ ማኅበረሰብ አባላት ወደ ቻይና የሚያደርጉት ጉዞ በወረርሽኙ ሳቢያ መስተጓጎል ገጥሞታል። በውጭ የሚኖሩ ቻይናውያንም በወረርሽኙ ምክንያት እንደልባቸው ተመላልሰው የአገራቸውንና የወገናቸውን ናፍቆት መወጣት እንዳይችሉ ሆነዋል። በተለያዩ አጋጣሚዎች ቀርበን ያወጋናቸው የአገሪቱ ባለሥልጣናት ቻይና ቁጥጥሩን በእጅጉ ብታላላው በርካታ ዜጓቿን በሞት ልታጣ እንደምትችል ጥናት አጣቅሰው አስረድተውናል። በመሆኑም ወረርሽኙን ለመከላከል የተተገበረው ፖሊሲ አገሪቱ ውድ የሆነውን የዜጎቿን ህይወት እንድታተርፍ ከማስቻሉ ባለፈ ምጣኔ ሀብታዊ ዕድገቷ ተጽዕኖዎችን ተቋቁሞ በአዎንታዊ የዕድገት ምህዋር ውስጥ እንድትገሰግስ እንዳስቻላትም ያትታሉ። ያም ሆኖ አገሪቱ ወረርሽኙን ለመከላከል የመደበችው የሰው ኃይልና የምታፈሰው ገንዘብ እጅግ በርካታ መሆኑን ሳስብ እንዲሁም ሕዝቡም ሳያወላውል ወረርሽኙን ለመግታት የወጡ ደንቦችን በማክበርና በመተግበር የተወጣው አስተዋፅኦ እጅግ ያስገርማል። ወረርሽኙን ለመከላከል የሄዱበት ርቀት ኢትዮጵያን ጨምሮ በበርካታ አገራት ለመከወን የሚቻልም አይደለም። ወደ ቀድሞ ነገር ስንመለስ- በዚህ አውድ ውስጥ የተካሄደው ይህ የጋዜጠኞች ሥልጠና በመደበኛነት የቻይና ታሪክ፣ ባህል፣ ማኅበራዊ አወቃቀር፣ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ፣ ፖለቲካዊ ሥርዓትና በአንዳንድ የጋዜጠኝነት ርዕሰ- ጉዳዮች ላይ ትኩረት ያደረገ ነበር። በተለይም የቻይናን አሁናዊ ሁኔታ እንድንረዳ ያለመ ሲሆን ወረርሽኙን ታሳቢ በማድረግም በሰሜኑና ደቡባዊ የአገሪቱ ክፍል በሚገኙ አምስት ግዙፍ ከተሞች ጉብኝት አድርገናል። በጎበኘናቸው እያንዳንዱ ከተሞች እጅግ የሚያስደምሙ የመንገድ፣ የወደብ፣ የኤርፖርት፣ የባቡር መስመርና ጣቢያ፣ መዝናኛ ሥፍራዎችና ሕዝባዊ ተቋማት የመሰሉ አስደማሚ መሰረተ-ልማቶችን ተመልክተናል። የኢንዱስትሪ ልማትና ስፋት፣ የቴክኖሎጂ ተደራሽነትና የተቋማት ግንባታው ቀልብን ይገዛል። የከተሞቻቸው ስፋትና መሰረተ-ልማት እንዲሁም ሌሎች የአገልግሎት አቅርቦቶች ዜጎቻቸው በምቹ ሁኔታ ውስጥ እንዲኖሩ አስችሏቸዋል። በጎበኘናቸው የገጠር አካባቢዎችም ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂ በመጠቀም ዜጎች ምርትና ምርታማነትን እንዲጨምሩ የሚሰራውን ሥራ በዚያው ልክም ገቢያቸው እያደገ የተሻለ ህይወት እየመሩ መሆኑን ተመልክተናል። በሌላ በኩል በቴክኖሎጂ ዘርፍ በተለይም በፈጠራ ሥራ አስደማሚ ሥራዎችን በመሥራት አገራቸው ሌላ ገጽታ እንዲኖራት ማስቻላቸውንም እንዲሁ። የቻይና ዕድገት የቻይና ዕድገት ከማንም የተሸሸገ ባይሆንም “ማየት ማመን ነው” እንደሚባለው በአካል ተገኝቶ አሁን ላይ አገሪቷ የደረሰችበትንና ቀድሞ የነበረችበትን ሁኔታ ማነጻጸር መቻል በራሱ ብዙ ያስተምራል። ቻይና ባለፉት 40 ዓመታት 800 ሚሊዮን ሰዎችን ከድህነት በማላቀቅ ቀዳሚ ተደርጋ የምትነሳ አገር ናት። በ1960ዎቹ አገራዊ ጠቅላላ ምርቷ ከጎረቤት አገራችን ከኬንያ በታች የነበረ ሲሆን፤ ከ1970ዎቹ ጀምሮ በአማካኝ 9 በመቶ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት በማስመዝገብ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2021፤ 17 ነጥብ 73 ትሪሊየን ዶላር ጠቅላላ አገራዊ ምርት በመያዝ ከአሜሪካ ቀጥላ ሁለተኛዋ ባለ ግዙፍ ኢኮኖሚ ባለቤት ለመሆን በቅታለች። እጅግ የከፋ ድህነት ውስጥ የነበሩት ቻይናውያን አሁን ላይ የነፍስ ወከፍ ገቢያቸው 10 ሺህ ዶላር ደርሷል። ቻይና በቀጣይ 13 ዓመታት የዜጎችን ገቢ 20 ሺህ ዶላር ለማድረስ ያለመታከት እየለፋች ትገኛለች። ቻይና አሁን እየሄደች ያለችበት የዕድገት ፍጥነት በተለይም ጠቅላላ የአገራዊ ምርት ደረጃዋ አሥር ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የአንደኝነት ደረጃን ከአሜሪካ እንድትረከብ ያስችላታል የሚሉ በርካታ ተንታኞች አሉ። በተቃራኒው በ1990ዎቹ ጃፓንም አሜሪካን በዕድገት ትቀድማለች ተብሎ ሳይሳካ መቅረቱን አንስተው፤ ይህንን መላምት ውድቅ የሚያደርጉ ተከራካሪዎችም አሉ። የቻይና ምጣኔ ሀብታዊ ግስጋሴ በጣም ፈጣን የሚባልና ለበርካታ ዓመታት የዘለቀ መሆኑ በዘርፉ ብቸኛዋ አገር ያደርጋታል። በተለይም ከሁለት ዓመታት በፊት የተቀሰቀሰው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ ምጣኔ ሀብቷን እስኪፈትነው ድረስ የአገሪቱ የዕድገት ሂደት ወጥ የሚባል ነበር ማለት ይቻላል። ቻይና እንዴት አደገች? ለሚለው ጥያቄ በርካታ የመስኩ ተንታኞች እንደሚያስቀምጡት፤ የቻይና ዕድገት “የኢንዱስትሪ መር” መሆኑን ያለልዩነት ይስማሙበታል። የቻይና መንግሥት አገሪቱን ለውጭ ገበያ እንዲሁም ለውድድር ክፍት ካደረገበት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ከ1978 ጀምሮ ከጥቃቅንና አነስተኛ ኢንዱስትሪዎች ጀምሮ አሁን ላይ እስከተገነቡ ግዙፍ ኩባንያዎች ድረስ ለኢንዱስትሪ ልማት የተሰጠው ትኩረት እጅጉን የሚያስገርም ነው። አገሪቱ በተለይም በገጠሩ የማኅበረሰብ ክፍል የግብርና ምርትን በማስፋፋት ለአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ የምርት ሽያጭ ዋጋን ከፍ በማድረግ ትልቅ ሥራ ሰርታለች። በአነስተኛ ኢንዱስትሪዎች የተጀመረው የኢንዱስትሪ ማስፋፊያ መርሃ-ግብርም ትልቅ እመርታን ማስመዝገብ አስችሏል። የኢንዱስትሪ ምርቶች የገበያ ተደራሽነታቸውን በማስፋት መንግሥት የሰጠው ከለላም ኢንዱስትሪዎቹ በእጅጉ እንዲያድጉ አድርጓል። ከዚያ በመለስ የቻይና የልማት ዕቅድ ውስጥ “ፈጠራ” ትልቅ ትኩረት የሚሰጠው ሲሆን የኢንዱስትሪና የምርምር ተቋማት በዚሁ ጉዳይ ላይ እንዲሰሩና የተሻሉ ውጤቶችን እንዲያመጡ አስችሏቸዋል። ዛሬ ላይ የቻይና ኢንዱስትሪዎች የውስጥ ፍላጎትን ከማዳረስ አልፈው ለሌሎች የዓለም አገራትም ተርፈዋል። በፈጠራ ሥራ ላይ ያስመዘገቧቸው ለውጦችም በተለይም በታዳጊ አገራት ላይ ቻይና ያላት ተጽዕኖ ከፍተኛ እንዲሆን አስችሏል። በሌላ በኩል ቻይና ጠንካራ መንግሥታዊ አመራርና ተከታታይነት ያለው ፖሊሲ ተግባራዊ በማድረጓ ለዚሁ መብቃቷም ይጠቀሳል። የሕዝቡ ፅናትና ቆራጥነትም ለዚህ ውጤት ጉልህ ሚና አለው። በተለይም ከ1970ዎቹ በፊት በነበሩት ጊዜያት የነበረው ድህነት ከባድ መሆኑን በማንሳት ቻይናውያን አንድም ወደ እዚያ ሕይወት ዳግም ላለመመለስና ያሉበትን ነባራዊ ሁኔታ ለመቀየር የነበራቸው ተነሳሽነት በሌላ በኩል ደግሞ ለቀጣይም ትውልድ የተሻለ አገር ለማስረከብ የነበራቸውን ቁርጠኝነት ለዕድገታቸው በምክንያትነት ያነሳሉ። ምን እንማር መቼም ከድህነት እስካልወጣንና የራሳችንን ዕድገት በራሳችን ጥረት እስካላረጋገጥን ድረስ ከአደጉ አገራት የመማራችን ሂደት ቀጣይነት ይኖረዋል። በእርግጥ አድገንም ቢሆን እስከጠቀመ ድረስ ከሌላ መማሩ አይጎዳም። ኢትዮጵያ የ3 ሺህ ዓመታት ታሪክ እንዲሁም ረዥም የመንግሥት አስተዳደር ታሪክ ያላት መሆኑን የራሳችንም የውጭ መጻህፍት ድርሳናትም ያስረዳሉ። በአንጻሩ ድህነትና ኋላቀርነትም ለበርካታ ዘመናት አሁንም ድረስ እግር በእግር እየተከተለ የዛሬይቷን ኢትዮጵያ መፈተኑ አልቀረም። በተለይም ለዘመናት የዘለቁ የጦርነት ጊዜያትና በፖለቲካው መስክ ያሉ ስንጥቃቶች ዛሬም ድረስ ተጽዕኗቸው እጅግ የጎላ ነው። ምንም እንኳን እንዲህ ያሉ የተዋረሱ ችግሮች አሉታዊ ተጽዕኗቸው በሁሉም ዘርፎች ላይ ቢሆንም በተለይም በምጣኔ ሀብት ረገድ አገሪቱ ፈቅ እንዳትል አድርጓታል። ያለፈው ታሪካችን አሁን ላይ ተጽዕኖው እንዳለ ሆኖ መጪው ጊዜ በሕይወታችን የሚያጓጓና ትልቁን ሥፍራ መያዙ አይቀሬ መሆኑን በመረዳት የተሻለች ኢትዮጵያን በኅብረት ለመገንባት ቆርጦ መነሳት ያሻል። በዚህ ረገድ በተለይም የቻይና ዕድገት ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለሌሎች አገራትም ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ ነው። ምንም እንኳን የተከተሉትን የኢኮኖሚ ሞዴል ጠቅልሎ ገቢራዊ ማድረግ ባይቻልም ቢያንስ ለበርካታ አገራት ሊሰራ የሚችለውንና የኢትዮጵያ መንግሥት አሁን ላይ ተግባራዊ በማድረግ ላይ የሚገኘውን በኢኮኖሚው መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችሉ ተግባራትን አጠናክሮ መቀጠል ይገባል። በተለይም ግብርናውን ማዘመንና የኢንዱስትሪ ልማትን ሊያስፋፉ የሚችሉ እንደ ጥቃቅንና አነስተኛ የመሰሉ ተቋማት በስፋት ማደራጀትና ወደ ተግባር ማስገባት ያስፈልጋል። በውስጣቸውም የሕዝቡን ህይወት ሊቀይሩ የሚችሉ ተጨባጭ የፈጠራ ሥራዎች እንዲስፋፉ የሚያስችሉ በፖሊሲ የተደገፉ ሥራዎችን መሥራት ግድ ይላል። ጎን ለጎንም ሕዝቡን በማንቃትና በማደራጀት ለአንድ አገራዊ ዓላማ እንዲሰለፍ ማድረግ ሌላው ከቻይና የምንማረው ጉዳይ ነው እላለሁ። አሁን ላይ በተለያዩ የፖለቲካ አጀንዳዎች ተጠምዶ ቀን ከሌት የሚያሰላስለውን ወጣት ወደ ልማት ፊቱን እንዲያዞር የሚያስችሉ ሥራዎች መሥራት ያሻል እላለሁ። በዚህ ላይ መንግሥት ብቻ ሳይሆን የአሁኗና የወደፊቷ ኢትዮጵያ የምትገዳቸው አገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን የወል ኃላፊነት መሆኑንም ልብ ይሏል። አብዝተው ስለ ራሳቸውና ስለቤተሰባቸው ከፍ ሲልም ማኅበረሰብንና አገራቸውን በሚጠቅሙና የጋራ ረብ ባላቸው ጉዳዮች ላይ ትኩረት የሚያደርጉ ባለ ራዕይ ወጣቶች ያስፈልጉናል። በበርካታ ጉዳዮች ላይ ብዙ ማለት ቢቻልም ጽሑፌን እዚህ ጋር ገትቼ ኢትዮጵያም እንደ እስያ ቻይና አድጋ ተመንድጋ እንድናያት እወዳለሁ።
የኤሌክትሪክ ኃይል-አንድም ብርሀን አንድም ቀጣናዊ ትስስር መፍጠሪያ መሳሪያ
Dec 5, 2022 235
የኤሌክትሪክ ኃይል አንድም ብርሀን አንድም ቀጣናዊ ትስስር መፍጠሪያ መሳሪያ (በሰለሞን ተሰራ) የአፍሪካ ቀንድ አለመረጋጋት የሚስተዋልበት በመሆኑ በአካባቢው በሚገኙ አገራት መካከል ጠንካራና ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት ለመመስረት አዳጋች ሆኖ ቆይቷል። አካባቢው ለዘመናት የዘለቀ አለመረጋጋት የሰፈነበት ከመሆኑ ጋር በተያያዘ ደካማ የሆነ የፖለቲካ አብሮነት ሲንጻባረቅበት የቆየ መሆኑን የፖለቲካ ተንታኞች ይስማሙበታል። ቀጣናው ከኢኮኖሚ ትብብር ይልቅ ወታደራዊ ትብብር የሚጎላበት፣ የአንድን አገር የውስጥ ሰላም ለማደፍረስ የተለያዩ አገራት ረጃጅም እጆቻቸውን የሚዘረጉበት፣ አገራት በጎረቤቶቻቸው ላይ ሴራ የሚጠነስሱበት እንደነበርም በቻታም ሀውስ የአፍሪካ ፕሮግራም ተባባሪ ተመራማሪና የጥናት ተንታኝ የሆኑት ሳሊ ሄሊ የተባሉ የፖለቲካ ምሁር ይጠቅሳሉ። በዚህም በቀጣናው የሚስተዋለው የእርስ በርስ ግጭት፣ አለመረጋጋትና የኢኮኖሚ ዕድገት ከማጓተቱ ባለፈ አገራቱ እርስ በርሳቸው እንዳይተማመኑ አድርጓቸው ቆይቷል። ሳሊ ሄሊ እንደሚሉት በአገራቱ ውስጥ የሚኖሩ ተመሳሳይ ማህበረሰቦች በርካታ በመሆናቸው በአንዱ አገር የሚፈጠረው የደህንነት ስጋት ሌላኛውን በቀጥታ ይጎዳዋል። ማህበረሰቦቹ አንድ አይነት የአኗኗር ባህል የተላበሱ በመሆኑ የመኖር ህልውናቸውም ሆነ ብልጽግናቸው ተነጣጥሎ የሚታይ አይደለም። ኢትዮጵያ በቀጣናው ከሚገኙ ሁሉም አገራት ጋር ድንበር የምትጋራ በመሆኑ የስጋቱ ቀጥተኛ ተጠቂ ናት። ይህን ተከትሎ ስጋቱን ወደ መልካም ዕድል ለመቀየር የተለያዩ የዲፕሎማሲ መስመሮችን በመዘርጋት የቀጣናውን ትስስር ጠንካራና ዘላቂ ለማድረግ እየሰራች ትገኛለች። በአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና የኢኮኖሚ ትስስር ለመፍጠርና የአፍሪካ ሕብረት ለአህጉሪቱ ልማት፣ ሰላምና ውህደት መሳሪያ ሊሆን የሚችልበት ሁኔታ እንዲጠናከር ለማስቻል በርካታ ሥራዎች ተሰርተዋል። ኢትዮጵያ በ”ኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ” ላይ የተመሰረተ ግንኙነት እንዲኖርና የጋራ ልማትና ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ በመትጋትም አርአያነቷን እያሳየች ትገኛለች። ከጎረቤቶቿ ጋር በወደብ፣ በባቡርና በየብስ ትራንስፖርት እንዲሁም የጋራ ተጠቃሚነትን በሚያጎለብቱ አያሌ መሠረተ ልማቶች ከመተሳሰር ባለፈ በቀጣናው ብሎም በአፍሪካ ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ የምታደርገው ጥረት በአርአያነት እንድትጠቀስ አድርጓታል። ነገር ግን ከአፍሪካ ቀንድና ከጎረቤት አገራት ጋር ቀጣናዊ ትስስር ለመፍጠር የምታደርገው ጥረት ያልተዋጠላቸውና የቀጣናው መረጋጋት ጥቅማችንን ያሳጣናል ብለው የሚያስቡ አንዳንድ ኃያላን አገራት በኢትዮጵያ ላይ የተለያዩ ጫናዎችን በማሳደር አገሪቱ ከያዛቸው ግብ ወደ ኋላ ለመሳብ እየተንቀሳቀሱ መሆኑ በግልጽ ይስተዋላል። ጫናዎቹ እንዳሉ ቢሆንም ኢትዮጵያ ግን ከትብብርና አብሮ መልማት አካሄዷ ዝንፍ አላለችም። ቀጣናውን በኢኮኖሚ ልማትና ዕድገት ለማስተሳሰር የወጠነችውን ግብ ለማሳካት ያግዛት ዘንድ ለጎረቤት አገራት የኤሌክትሪክ ኃይል ለማቅረብ የጀመረችውን ጥረት ገፍታበታለች። ለአብነትም የውሃ፣ ነፋስ፣ እንፋሎትና የጸሃይ ብርሃን በመጠቀም ኃይል አምራች በመሆን ከምስራቅ አፍሪካ ባሻገር የአፍሪካ የኃይል ምንጭ ማዕከል ለመሆን ግብ ጥላ እየተንቀሳቀሰች ትገኛለች። የኃይል አቅርቦት ጅማሮው በምስራቅ አፍሪካ አገራት መካከል ድንበር ዘለል የሃይል ንግድ እንዲሁም ትስስርን ለማጎልበት ያግዛል። ይህም በአውሮፓውያኑ ዘመን አቆጣጣር 2005 የተቋቋመው ኢስተርን አፍሪካ ፓወር ፑል እንቅስቃሴ ተግባራዊነት የሚያረጋግጥ ነው። ኢስተርን አፍሪካ ፓወር ፑል ምስራቅ አፍሪካን በአስተማማኝና ዘመናዊ የኃይል አገልግሎት ተደራሽ በማድረግ በዓለም ላይ ካሉ ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻዎች አንዱ ተብሎ ወደሚታወቅ ቀጣና የመቀየር ራዕይ አለው። በአጠቃላይ የኃይል ልማትን የማስተባበር ስልጣን የተሰጠው የተቋሙ ዋና ፅህፈት ቤት በአዲስ አበባ የሚገኝ ሲሆን አስራ አንድ አባል አገራት አሉት። አገራቱም ግብፅ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሱዳን፣ ታንዛንያ፣ ኡጋንዳ፣ ሊቢያ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ሩዋንዳ፣ ደቡብ ሱዳን እና ሶማሊያ ናቸው። ይህን የምስራቅ አፍሪካ የኃይል ፖል ኢኒሸቲቭን መሰረት አድርጋ የምትንቀሳቀሰው ኢትዮጵያ በቀጣናው ለሚገኙ በርካታ አገራት የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽ በማድረግ ላይ ትገኛለች። አሁን ላይ ለኬኒያ፣ ሱዳን፣ ጅቡቲ ኃይል የምታቀርብ ሲሆን በቀጣይ ለታንዛኒያ፣ ሩዋንዳ፣ ደቡብ ሱዳን ኃይል በማቅረብ ምስራቅ አፍሪካን በልማት ለማስተሳሰር እየተጋች ነው፡፡ በቀጣይ ዓመታትም የኃይል ምርትና የአቅርቦት ምጣኔዋን በማሳደግ የምስራቅ አፍሪካ ቀዳሚዋ የኃይል አቅራቢ ለመሆን እየሰራች ነው። ኢትዮጵያ ለጂቡቲ፣ ኬንያና ሱዳን የኤሌክትሪክ ኃይል የምትሸጥበት ታሪፍ ተቀራራቢነት ያለው ሲሆን በዋናነት የጋራ የልማት ትስስርን መሰረት ያደረገ ነው። በ2014 ዓ.ም. ባለፉት ዘጠኝ ወራት ለጅቡቲ 527 ጊጋ ዋት ሰዓት ኃይል ለማቅረብ ታቅዶ 611 ጊጋ ዋት ሰዓት ማቅረብ የተቻለ ሲሆን ለሱዳን ደግሞ 1 ሺሕ 93 ጊጋ ዋት ሰዓት ማቅረብ መቻሉን መረጃዎች ያመለክታሉ። መንግስት ለጅቡቲና ሱዳን ካቀረበው የኃይል ሽያጭ ያገኘው 95 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ሲሆን፤ ካለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀርም የ4 ነጥብ 9 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ወይም የ5 ነጥብ 4 በመቶ ጭማሪ እንዳለውና የአገራቱ ትስስር እየጎለበተ መምጣቱን ያሳያል። አገራቱ ካለባቸው የኃይል እጥረት አኳያ የኢትዮጵያ በጋራ የመልማት አካሄድ ተጠቃሚ እያደረጋቸው ይገኛል። በተለይ ጅቡቲ ኃይል ለማመንጨት ለድንጋይ ከሰልና ለነዳጅ የምታወጣውን ወጪ በከፍተኛ ደረጃ በመቀነስ ከስምምነቱ በእጅጉ ተጠቃሚ ያደርጋታል። ሱዳን ከዚህ ቀደም ወደ 200 ሜጋ ዋት የሚጠጋ የኤሌክትሪክ ኃይል ከኢትዮጵያ እንደገዛችና ይህም የሱዳንን 10 በመቶ የኤሌክትሪክ ሀይል ፍላጎትን እንደሚሸፍን የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃን ጠቁመዋል። በተመሳሳይ ኢትዮጵያና ኬንያ በኃይል ለመተሳሰር የጀመሩት ጉዞ በቅርቡ ለፍሬ በቅቷል። በ2008 ዓ.ም. ግንባታው የተጀመረው የኢትዮ-ኬንያ የኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ መስመር ዝርጋታ 1 ሺ 068 ኪ.ሜ ርዝመት ያለው ሲሆን፣ አጠቃላይ ፕሮጀክቱ 1 ነጥብ 26 ቢሊዮን ዶላር ወጥቶበታል። የማስተላለፊያ መስመሩ በኢትዮጵያ በኩል 437 ኪ.ሜ በኬኒያ በኩል ደግሞ 631 ኪ.ሜ. ርዝመት አለው። በኢትዮጵያ በኩል የተዘረጋው መስመር ከወላይታ-ሶዶ ማከፋፈያ ጣቢያ ጀምሮ አርባ ምንጭ፣ ኮንሶ፣ ብርንዳር፣ ያቤሎና ሜጋንን አቋርጦ ኬንያ የሚዘለቅ ሲሆን ግንባታው በመጠናቀቁ ኢትዮጵያ ለኬኒያ ኃይል ማቅረብ ጀምራለች። ኢትዮጵያ በቀጣይ ዓመታት ለሩዋንዳ፣ ለታንዛኒያና ለብሩንዲ የኤሌክትሪክ ኃይል ለመሸጥ ውይይት የጀመረች በመሆኑ የኬንያው መስመር ዝርጋታ ለኤሌክትሪክ ኃይል ሽያጭ ትልቅ ሚና ይኖረዋል። አዲስ የተገነቡትና በመገንባት ላይ የሚገኙት እንደ ግልገል ጊቤ 3፣ ኮይሻና ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ስኬቱን ለማፋጠን አጋዥ ተደርገው ይቆጠራሉ። የታዳሽ ኃይል አቅርቦት ቀጣናውን በኃይል ከማስተሳሰር ባለፈ የአፍሪካ ቀንድ አገራት ስጋት የሆነውን የአየር ፀባይ ለውጥ ለመከላከል የራሱን አስተዋጽኦ ያበረክታል። ወደ ጎረቤት አገር የሚላኩት የኤሌክትሪክ ኃይልና የወጭ ንግድ ምርቶች ኢትዮጵያ በኢጋድ አገሮች ውስጥ ለሚኖረው አካባቢያዊ ትስስር የሰጠችውን ከፍተኛ ትኩረት ያመለክታል። በዚህም ከኃይል አቅርቦቱ ባለፈ በኢትዮጵያ በኩል አልፈው ወደ ኬንያ፣ ሶማሌላንድ፣ ሱዳን፣ ደቡብ ሱዳንና ጂቡቲ የሚዘልቁ ከ13 በላይ የመገናኛ ኮሪደሮች ይገኛሉ። ኢትዮጵያ በኢኮኖሚያዊ ዲፕሎማሲ ረገድ የምታደርገውን እንቅስቃሴ በሚያግዝ አግባብ ሰፊ መዋለ ንዋይ በማፍሰስ መሰረተ ልማቶችን በማስፋፋት ላይ ትገኛለች። በመንገድ፣ በባቡር፣ በነጻ የንግድ ቀጣና፣ በኃይል ትስስር እየሰራቻቸው ያሉ ስራዎች በአብነት የሚጠቀሱ ናቸው። አገሪቷን በአገር ውስጥና በክፍለ አህጉሩ ደረጃ ለማገናኘት የሚያግዝ 4 ሺ 744 ኪሎ ሜትር የሃዲድ መስመር የሚሸፍን ስምንት የባቡር መንገድ ኮሪደሮች በሁለት ምዕራፍ ለመገንባት የተያዘው ዕቅድ ሌላው ማሳያ ተደርጎ ሊነሳ ይችላል። የኢትዮጵያ የገቢ ሸቀጥ 90 በመቶ በጅቡቲ ስለሚገባ የኃይል አቅርቦቱ ይህንኑ የወደብ እንቅስቃሴ ለማሳለጥና የህዝቦችን ኢኮኖሚያዊና የአገራቱን የጋራ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ያለው ሚና ወሳኝ ነው። ቀጣናው በአየር ጸባይ ለውጥ የተነሳ ለተደጋጋሚ ረሃብ፣ ድርቅ፣ ጎርፍና የአንበጣ ወረረርሽኝ የተጋለጠ በመሆኑ የታዳሽ ኃይል ግንባታ ጥረቱ በመጠንም ቢሆን እነዚህን ስጋቶች እንደሚያስወግድ ታምኖበታል። ኢትዮጵያ ለአየር ጸባይ ለውጥ ምክንያት ባትሆንም የችግሩ ሰለባ ከሆኑ ግንባር ቀደም የምስራቅ አፍሪካ አገራት አንዷ ናት። የታዳሽ ኃይል አቅርቦቱ በአፍሪካ ቀንድ አገራት የስራ ዕድል በመፍጠር፣ ከባቢያዊ ሁኔታን በመጠበቅና የደን ሃብትን ከውድመት በመታደግ የራሱ የሆነ ኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። ከዚህ ባለፈ ትስስሩ የአገራቱ የፖለቲካና የለውጥ መሰረት ለሆነው አገር ተረካቢ ወጣት ዘርፈ ብዙ የስራ ዕድል በመፍጠር ትውልዱን ከስጋት ምንጭነት ወደ ልማት ፊት አውራሪነት ለመቀየር ያስችላል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ኢነርጂ ማዕከል ለመሆን በያዘችው እቅድ የውሃ፣ የነፋስ፣ የእንፋሎት እና የጸሃይ ብርሃን ሀይል የማመንጨት አቅሟን ለማሳደግ እየሰራች ትገኛለች። ይህም ንጹህ ኢነርጂን በመጠቀም ረገድ በዓለም ላይ ትልቅ የፖሊሲ ለውጥን የሚያሳይ እንዲሁም ኢትዮጵያን በአፍሪካ ንጹህ ኢነርጂን በመጠቀም ቀዳሚ እንድትሆን እንደሚያስችላት ተገልጿል። ይህም ከቀጣናው ባለፈ አፍሪካን በኃይል አቅርቦት ለማስተሳሰር የጀመረችውን ቁርጠኛ አካሄድ ያረጋግጣል። በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የተዘጋጀው የ2013-2022 የአስር ዓመት የልማት ዕቅድ ላይ እንደተመላከተው በአገር ውስጥ ያለውን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተደራሽነት ከማረጋገጥ በተጨማሪ ዓለም አቀፍ የጥራት መስፈርቶችን የሚያሟላ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ለጎረቤት አገራት ማቅረብን ታሳቢ ያደረገ ነው። ይህም ኢትዮጵያ ጎረቤትን ያስቀደመ በጋራ የመልማት አካሄዷ ማሳያ ብቻ ሳይሆን ማረጋገጫ መሆኑን ከልማት ዕቅዱ ተጨልፈው በጥቂት ዓመታት ውስጥ የተከናወኑና ለውጤት የበቁ የልማት ስራዎች ምስክሮች ናቸው። እነዚህን ትስስሮች በማጎልበት መተማመንን የሚፈጥሩ ተግባራት ማጠናከርና በጋራ በመልማት መርህ ላይ ተመስርቶ መስራት የሁሉም አገራት ቀዳሚ አማራጭ ሊሆን ይገባል።
ለዓለም ዋንጫ ባታልፍም በውድድሩ ሁሉም ጨዋታዎች ላይ የምትሳተፈው ኢንዶኔዢያ
Nov 28, 2022 234
ኢንዶኔዢያ በ22ኛው የኳታሩ የዓለም ዋንጫ ካልተሳተፉ ሀገራት መካከል ብትሆንም በውድድሩ ሁሉም ጨዋታዎች በሚባል ደረጃ እየተሳተፈች ነው። በዓለም ዋንጫ ውድድሩ ሳይሳተፉ ኢንዶኔዢያን በውድድር በመወከል ታሪክ የሰሩት ዜጎቿም “በጣም ኩራት ተሰምቶናል” ሲሉ ለሀገራቸው ክብር የበኩላቸውን በማድረጋቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። ለኢንዶኔዢያ ኩራት የሆነውን ጉዳይ በተመለከተ ዘገባ የሰራው አልጀዚራ የኢንዶኔዢያ ልጆች ሀገራቸውን ለዓለም ዋንጫ ማሳለፍ ባይችሉም በኳስ ምርታቸው ግን በውድደሩ ተፋላሚ ሆነዋል ብሏል። ሀገሪቷ የውድድሩ ተሳታፊነትን ያገኘችው በምሥራቅ ኢንዶኔዢያ ማዲየም በተባለች ግዛት በሚገኘው ፒቲ ግሎባል ዌይ በተሰኘ ኩባንያ አማካኝነት ነው። ኩባንያው በኳታሩ የዓለም ዋንጫ ጨዋታ ላይ “አል ሪህላ” በሚል ስያሜ የሚቀርበውን ኳስ እንደሚያመርት እ.አ.አ በ2020 መገለጹ ይታወቃል። በዛው ዓመት ኩባንያው ቅርንጫፉን በግዛቲቱ በመክፈትም በዓለም ዋንጫው ያልተሳተፉ ኢንዶኔዢያውያን በኳታሩ የዓለም ዋንጫ አሻራቸውን እንዲያኖሩ እድል ፈጠረላቸው። የማዲየም ግዛት አስተዳዳሪ አህመድ ዳዋሚ በሰጡት አስተያየት” አል ሪህላ የኩራት ምንጭ ሆኖናል በተጨማሪም ወደ ኳሱ ምርት ከገባንበት ጊዜ ጀምሮ ለሀገር ውስጥ የገቢ ምንጫችን ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል” ብለዋል። የኢንዶኔዢያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርም የማዲየም ግዛት ነዋሪዎች “በኳታሩ ዓለም ዋንጫ ውድድር ላይ ሀገሪቱን በኳስ ምርት በማሳተፍና ገቢን በማመንጨት የዓለም ኢኮኖሚ አንድ አካል ሆነዋል” ሲል ኢንዶኔዢያ ከተሳትፎ ባሻገር ከዓለም ዋንጫው ያገኘችውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅምና ለውድድር ያበረከተችውን አስተዋጽኦ ገልጿል። ጉዞ የሚል ትረጉምን የያዘው የዓለም ዋንጫው ኳስ “አል ሪህላ” ከአዲዳስ ኩባንያ ጋር በጥምረት የሚመረት ሲሆን በፊፋ የደረጃ ምደባም 14ተኛው ይፋዊ የዓለም ዋንጫ ኳስ መሆኑም ተመልክቷል። አል ሪህላ በዓለም ዋንጫ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የአካባቢ ብክለትን መከላከል አንዲችል ሆኖ ውሃማ መሠረት ካለው ሙጫና ቀለም የተሰራ መሆኑ በዘገባው ተካቷል። በቅርብ ዓመታት በተካሄዱ የዓለም ዋንጫ ውድድሮች ጥቅም ላይ ከዋሉት ኳሶች መካከል የ2006ቱ ቴሜጊይስት በርሊን፣ በ2010 ደቡብ አፍሪካ ባዘጋጀችው የዓለም ዋንጫ ጥቅም ላይ የዋለችው ኳስ ጃቡላኒ የሚል ስያሜ የተሰጣት ሲሆን በሴቶች ብቻ የተመረተ ስፒድ ሴል፣ የ2014 ቱ ብራዙካ እና የ2018 ቱ ቴልስታር ይጠቀሳሉ።
ከስደት መልስ - አገር አቀፍ የግብርና ዘር አምራች ካምፓኒ የመመስረት የታታሪነት ጉዞ
Nov 12, 2022 286
ዑመር መሀመድ አወል ይባላሉ፤ ውልደትና እድገታቸው ወልቄጤ ከተማ ሲሆን በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ ቦረር ሜዳ ቀበሌ የሚገኘው የ"መሀመድ አወል እርሻ ልማት" ባለቤትና ስራ አስኪያጅ ናቸው። በአገራቸው ላይ ሙአለ ንዋይ አፍስሰው መስራት ከመጀመራቸው በፊት ለ10 ዓመታት በስደት ኖረዋል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት ዑመር መሀመድ በ1987 ዓ.ም ወደ አሜሪካ በማቅናት በተለያዩ የስራ መስኮች ተሰማርተው ሲሰሩ እንደነበር አስታውሰዋል። በአገር ሰርቶ መለወጥ እንደሚቻል በማመንም በ1999 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ በቅተዋል። ትኩረታቸውንም አባታቸው መሀመድ አወል በ1985 ዓ.ም ያቋቋሙትን የእርሻ ልማት ድርጅት በማጠናከርና በማስፋፋት አገርና ወገናቸውን መጥቀም በሚችሉበት ጉዳይ ላይ አደረጉ። ጊዜ አልፈጁም ወዲያው ወደ ሰብል ልማትና ምርጥ ዘር ማምረት ተሸጋገሩ። ቀጥለውም በስራ ሂደት ሊያጋጥሙ የሚችሉ እንቅፋቶችን በመቋቋም በአገር ሰርቶ መለወጥ እንደሚቻል ማሳያ የሆነ የባለ ግዙፍ ምርጥ ዘር አምራች የእርሻ ልማት ድርጅት ባለቤትና ስራ አስኪያጅ ለመሆን እንደበቁ ይገልፃሉ። ከ30 ዓመታት በፊት 160 ሄክታር መሬት ከመንግስት በመረከብ የሰብል ልማት ስራውን አንድ ብሎ የጀመረው የእርሻ ልማት ድርጅት ዛሬ ላይ ከ1ሺ 400 ሄክታር በላይ መሬት ላይ በቆሎ፣ ቦሎቄ፣ ጤፍ፣ ሽምብራ እና ስንዴ በማምረት ላይ ይገኛል። በቅርቡም በደቡብ ክልል ርዕሰ-መስተዳድር ርስቱ ይርዳው የተመራ የፌደራልና የክልል የስራ ኃላፊዎች ቡድን በእርሻ ልማቱ እየተከናወነ የሚገኘውን የምርጥ ዘር ሰብል ልማት እንቅስቃሴ ጎብኝቷል። የእርሻ ልማቱ አገር ከምትሻው ሰፊ የምርጥ ዘር አቅርቦት በተጨማሪ 2ሺህ ለሚደርሱ ወገኖች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አቶ ዑመር ተናግረዋል። ለሰራተኞቹም እስከ 2 ሚሊየን ብር የሚደርስ ወርሃዊ ክፍያ እንደሚፈጸም ጠቅሰው ጠንክሮ መስራት ለዛሬ ውጤት እንዳበቃቸው ይናገራሉ። ከ2ሺህ ዓ.ም ጀምሮ ያካበቱትን የምርጥ ዘር ሰብል ልማት ተሞክሮ በበቆሎ ምርጥ ዘር ማሻሻያ ላይ ትኩረት በማድረግ እየሰሩ እንደሚገኙ ይጠቅሳሉ። በተያዘው ዓመትም የእርሻ ልማት ድርጅቱ መንግስት በምርጥ ዘር ሰብል ልማት እያከናወነ የሚገኘውን ስራ ለማገዝ "ሊሙ" የተሰኘን የበቆሎ ምርጥ ዘር እያለሙ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በምርጥ ዘር ማሻሻያ ልማት ስራውም በሄክታር እስከ 50 ኩንታል የሚደርስ የበቆሎ ምርጥ ዘር ምርት ለመሰብሰብ እየጠበቁ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የኢትዮጵያን የሰብል ምርጥ ዘር እጥረት ለመሙላት ድርጅቱ እያደረገ ባለው ጥረት የመንግስት እገዛ እንዳልተለያቸውም ያነሳሉ። በዚህም የተሻሻለ የበቆሎ ምርጥ ዘርን በማልማት የአርሶ አደሩን የምርጥ ዘር ፍላጎት ለመሙላት ሰፊ ስራ እያካሄደ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በእርሻ ልማት ድርጀቱ እየተካሄደ ከሚገኘው ሰፊ የበቆሎ ሰብል ምርጥ ዘር ብዜት በተጨማሪ ለ14 ሺህ አርሶ አደሮች የሚውል 7ሺህ ኩንታል የቀይ ቦለቄ ምርጥ ዘር ማምረት እንደተቻለ ጠቁመዋል። የአረንጓዴ አሻራ ልማትም ሌላኛው በድርጅቱ እየተከናወነ የሚገኝ የልማት ስራ እንደሆነ አንስተዋል። በቀጣይም አኩሪ አተርን ለማልማት እቅድ እንዳላቸው ጠቁመው፤ በመጪው የበጋ ወራትም ስንዴን በመስኖ ለማልማት ዝግጅት እያደረጉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሌሎች ባላሀብቶችም በእርሻ ኢንቨስትመንት ስራ በሚደረግ ጥረት ውጤት ማምጣት እንደሚቻል አማራጩን ማየት እንዳለባቸው መክረዋል። የመንገድ እና መሰል በልማት ሂደት የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመቋቋም ለአገራቸው ምርጥ ዘር አቅርቦት አሻራቸውን እያኖሩ እንዳሉ ተሞክሯቸውን በማጋራት። በሚቀጥሉት አስር ዓመታት ውስጥ "የመሀመድ አወል እርሻ ልማት" ድርጅት ግንባር ቀደም አገር ዓቀፍ የምርጥ ዘር አቅራቢ ድርጅት ለመሆን እየተጋ እንደሚገኝም አመላክተዋል። ድርጅቱ እያበለጸጋቸው የሚገኙ የሰብል ልማቶችም ትልቅ የተሻሻለ ምርጥ ዘር አቅራቢ ድርጅት እንደሚሆን አረጋግጠዋል።
አሊ ቢራ - የጸደይ ብርሃን አብሳሪ
Nov 7, 2022 408
(በአሸናፊ በድዬ) "ሰምቼ የማልጠግበው ድምጽ 'ዛሬ ዝም አለ' የሚል ዜና ሰማሁ። እንደሌላ ጊዜው ውሸት በሆነ ብዬ ተመኘሁ። ግን መራራ እውነት ነው። ባለወርቃማ ድምጹ አሊ ቢራ ትቶልን የሄደው ብዙ ነው።" ይህ አንድ የአንጋፋው አርቲስት አድናቂ ሀዘኑን የገለጠበት መንገድ ነው። እውነትም ክቡር ዶክተር አርቲስት ዓሊ ቢራ ከሙዚቃ ጋር ከስድስት አስርታት የበለጠ እድሜ የተቆራኘ መጠሪያውን ጭምር በጥበብ ስራው የተካ ድንቅ ሰው ነበር። የኢትዮጵያ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ዛሬ ለደረሰበት ደረጃ ባለውለታ ከሆኑ አንጋፋ ድምጻዊያን መካከል ዓሊ ቢራ በቀዳሚነት ከሚቀመጡት ይመደባል። በተለይም የአፋን ኦሮሞ ሙዚቃዎች ከፍ ብለው እንዲደመጡና በርካታ ሰዎች ጋር ተደራሽ እንዲሆኑ ከማድረግ አንጻር አሊ ቢራ የነበረው ሚና እጅግ ላቅ ያለ ነው፡፡ ሙዚቃ ቋንቋ ነው የሚለውን ብሂልም በተግባር አሳይቷል። ለአፋን ኦሮሞ ቋንቋ የሙዚቃ እድገትም ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል። በበርካታ ቋንቋዎች ሙዚቃን የሚጫወተው አሊ ቢራ በአፋን ኦሮሞ በተጫወታቸው በርካታ ሙዚቃዎቹ ዘመን ተሻጋሪና ተፅዕኖ ፈጣሪ መሆን በመቻሉ ትልቅ ስፋራ ይሰጠዋል፡፡ ይህ የሙዚቃ ሰው በድሬደዋ ገንደ ቆሬ ተብሎ በሚጠራው አከባቢ ከአባቱ መሐመድ ሙሳ እና ከእናቱ ፋጡማ አሊ በ1940 ዓ.ም ነው የተወለደው። ከህጻንነቱ ጀምሮም የተለያዩ የአገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ ሙዚቃዎችን እያደመጠና እያንጎራጎረ ማደጉ ይነገራል፡፡ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በድሬዳዋ ከተማ፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ደግሞ በአዲስ አበባ ካቴድራል ትምህርት ቤት ተከታትሏል። አሜሪካ አገር በሚገኘው የሳንታ ሞኒካ ኮሌጅም የሙዚቃ ትምህርት ተምሯል። አርቲስት ዓሊ ቢራ በ1954 ዓ.ም ገና በ13 ዓመቱ የኦሮሞን ሙዚቃ ለማስተዋወቅ ዓላማ አድረጎ የተቋቋመውን ባህላዊ የሙዚቃ ቡድን “አፍረን ቀሎ”ን በመቀላቀል ነው የሙዚቃ ስራውን አንድ ብሎ የጀመረው። አሊ ቢራ በዚህ የባህል ቡድን ተቀላቅሎ ለመጀመሪያ ጊዜ በመድረክ ያቀነቀነው ሙዚቃም የዛሬው የስሙ መጠሪያ የሆነው "ቢራ ዳ በሪኤ" የሚለው ሙዚቃ ነው፡፡ "ቢራ ዳ በሪኤ" የሚለው ሙዚቃ ከባዱ ክረምት አልፎ አዲስ ብርሃን መውጣቱን ገና በለጋ እድሜው በማብሰር የሙዚቃ ተስፋውንም አብሮ ያለመለመበት ነው። በዚህ ሙዚቃ ምክንያትም "አሊ መሐመድ ሙሳ" የነበረው ስሙ "አሊ ቢራ" ተብሎ እንዲጠራ አድርጎታል፡፡ ድምጻዊ ዓሊ ቢራ ከአፍ መፍቻ ቋንቋው ከአፋን ኦሮሞ በተጨማሪ በአማርኛ፣ በአረብኛ፣ በሃረሪ እና በሶማሊኛ ቋንቋዎች የመዝፈን ችሎታ አለው። በክብር ዘበኛ ኦርኬስትራ ተቀጥሮ ለሦስት ዓመታት የሰራ ሲሆን ‘አይቤክስ’ ባንድን በመቀላቀል ለስምንት ዓመታት የሙዚቃ ስራዎቹን በዲ አፍሪካ ሲያቀርብ መቆየቱም ይነገራል፡፡ ከ267 በላይ ሙዚቃዎች ያበረከተው ድምጣዊው በአፋን ኦሮሞ የሙዚቃ ታሪክ ውስጥ የመጀመሪያው የሆነውን አልበሙን በ1971 ዓ.ም ከመስራቱ በተጨማሪ ለገበያ የቀረቡ 13 አልበሞች እንዳሉትም በአንድ ወቅት ባደረገው ቃለ ምልልስ ተናግሯል፡፡ የክብር ዶክተር አሊ ቢራ የሙዚቃ ስራዎች አፋን ኦሮሞ በማይሰሙ ሰዎች ዘንድም ጭምር እጅግ ተቃባይነት ያላቸው መሆኑን ባለቤቱን ጨምሮ በርካቶች ምስክርነት ሰጥተዋል። እጅግ ተወዳጅ ከሆኑ ስራዎቹ መካከልም:- "Birraa dhaa Barihe" የመጀመሪያ ስራው፣ " Waa Malli nu dhibe"፣ "Jaalaluma teeti"፣ "Barnootaa"፣ "Ushuruururuu"፣ "Karaan Mana Abbaa Gadaa"፣ "Nin deema"፣ "Dabaala Keessan" የሰርግ ሙዚቃ፣ "Amalele" ከብዙዎቹ መካከል ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ድምጻዊ አሊ ቢራ "Waa Malli nu dhibe" በሚለው የሙዚቃ ስራው እናታችን አንድ ናት ምንድነው የሚያለያየን በማለት ኢትዮጵያዊያን አንድ መሆናቸውን እና መቼም መለያየት የማይችሉ የአንድ እናት ልጆች መሆናቸውን በሙዚቃ ስራው በማቀንቀን ከመለያየት ይልቅ አንድነት ፍቱን መፍትሄ መሆኑን አንጸባርቆበታል፡፡ "Karaan Mana Abbaa Gadaa" በሚለው የሙዚቃ ስራውም ፍትሃዊነት፣ እኩልነት፣ አንድነት፣ መልካምነት፣ ግልፀኝነት፣ ሀቀኝነት የገዳ ስርዓት መገለጫዎች ስለመሆናቸው አቀንቅኗል፡፡ "ትምህርት የሁሉም ነገር መፍቻ ቁልፍ ነው" ብሎ እንደሚያምን የሚናገረው ድምጻዊ አሊ ቢራ ትውልዱ ትኩረቱን ትምህርት ላይ ብቻ ማድረግ እንዳለበትም "Barnootaa ammas Barnootaa" በሚለው ሙዚቃ ስራው አስተምሯል፡፡ "Amalele ……….. an yaada keen takka hin bule" በማለት ስለፍቅር ሃያልነት ባቀነቀነው ሙዚቃ ፍቅር የሁሉም ነገር ማሰሪያ፣ ከደስታዎች ሁሉ በላይ ደስታ መሆኑም ለትውልዱ አስተምሯል፡፡ ድምጻዊ ዓሊ ቢራ ለኢትዮጵያ ህዝቦች አብሮነትና ማህበራዊ ትስስር ከፍ ያለ አስተዋጽኦ አበርክቷል። በሙዚቃዎቹ ዘመን ተሻጋሪ መልዕክቶችን በማስተላለፍ መልካም ትውልድ እንዲቀረጽ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል። የተለያዩ ፈተናዎችን ተሻግሮ በከፍተኛ ጽናትና ብቃት ለረጅም ዓመታት በኪነ ጥበቡ ውስጥ ያሳለፈ መሆኑ ደግሞ አሁን ላለው ትውልድ ታላቅ ተምሳሌት ያደርገዋል። በርካታ የሙዚቃ መሳሪያዎችን የሚጫወተው አሊ ቢራ ከአርባ በላይ በሆኑ አገራት እጅግ በርካታ የመድረክ የሙዚቃ ስራዎችን ተጫውቷል። ባለፉት 60 ዓመታት በኦሮሞ የሙዚቃ ስራዎች ውስጥ እንቁ ሆኖ የቆየ፣ በርካታ ወጣቶችን ማፍራት የቻለ፣ ትውልዱ በእውቀት እና በስነ-ምግባር እንዲቀረጽ በሙዚቃ ስራው ትልቅ አስተዋጽኦ ያደረገ ታላቅ የሙዚቃ ሰው ነው፡፡ ድምጻዊ ዓሊ ቢራ “Birra Children’s Education Fund” የተባለ ምግባረ ሰናይ ድርጅት ከባለቤቱ ጋር አቋቁመው ለሕፃናት ትምህርት ድጋፍ በመስጠት ላይ ይገኛሉ። በዘርፉ ላበረከተው ታላቅ አስተዋፅኦ ሁለት የክብር ዶክተሬት የተሰጠው አርቲስት ዓሊ ቢራ፣ ከአገር ውስጥና ከውጭ ሀገር ተቋማት የተለያዩ እውቅናዎችን እና ሽልማቶችን አግኝቷል። ለአብነትም ከድሬዳዋ እና ከጅማ ዩኒቨርስቲዎች የክብር ዶክትሬት ተበርክቶለታል፤ በድሬደዋ ከተማ ፓርክ እንዲሁም በአዳማ መንገድ በስሙ ተስይሟል፣ የኦሮሚያ ክልል በሙዚቃው ዘርፍ ላበረከተው አስተዋጽኦ ልዩ የኒሻን ሽልማት አበርክቶለታል፤ የመጀመሪያው የኢሬቻ የሰላም ሽልማት ተሸላሚም ሆኗል፤ የአርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳ የኪነጥበብ ሽልማት የህይወት ዘመን ተሸላሚ ለመሆንም በቅቷል፤ የኦሮሚያ ቱሪዝም ኮሚሽን ከፍተኛ ሽልማት አግኝቷል፤ በካናዳ ቶሮንቶ የአፍሪካ የምንጊዜም አንጋፋ ሙዚቀኛ ሽልማት አግኝቷል፤ የኦዳ አዋርድ የሕይወት ዘመን ተሸላሚ መሆን ችሏል፤ ሌሎችንም ከፍተኛ ማዕረጎችንና ሽልማቶች አግኝቷል፡፡ የአንጋፋውን አርቲስት የክቡር ዶክተር አሊ ቢራን ህልፈት ህይወት አስመልክቶ ብዙዎች ሀዘናቸውን ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ሀላፊዎች፣ የክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ የሙያ አጋሮቹ አገር ትልቅ ባለውለታዋን ማጣቷን ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ "የአንጋፋው ድምጻዊ ዓሊ ቢራ ህልፈት ለኢትዮጵያ ጉዳት ነው፤ በዜማዎቹ ኅብረትን፣ ጽናትንና ባህልን አቀንቅኗል፤ ለብዙዎችም አርአያ ሆኗል፤ ላደረግከው ሁሉ ኢትዮጵያ ታመሰግንሃለች" በማለት ሀዘናቸውን ገልጸዋል። ይህ አንጋፋ አርቲስት በህይወት ቢለየንም ህያው ስረዎቹ ግን አብረውን ይዘልቃሉ።
ታላቁ ዓሊ
Nov 7, 2022 210
በብርሃኑ አለማየሁ ዘመን በማይሽረው መረዋ ድምጹ አንድነትን፣ ፍቅርን፣ ኅብረትን፣ ጽናትንና ባህልን ያቀነቀነው ታላቁ ድምጻዊ አሊ መሀመድ ሙሳ ወይም በመድረክ ስሙ ዓሊ ቢራ የዘመናዊ የኦሮሚኛ ሙዚቃ ታሪክ ሲነሳ ትልቅ አስተዋጽኦ ካበረከቱ አቀንቃኞች መካከል ስሙ ከፍ ብሎ ይጠራል። አርቲስት ዓሊ ቢራ ከሀምሳ ዓመታት በላይ በተሻገረው የሙዚቃ ሕይወቱ ያልዳሰሰውና ያልነካው ጉዳይ የለም ይልቁኑም ስራዎቹ የአዛውንት ትዝታ፣ የወጣቶች ተስፋና የማህበረሰብ ማንቂያ ሆነዋል። ከአድማጭ ጆሮ ከወዳጆቹ አንደበት ሳይጠፉ በኢትዮጵያውያን ልብ በፍቅር የሚቀነቀኑት የዓሊ ሙዚቃዎች እርሱ ዛሬ በሕይወት ባይኖርም ትውልድ የሚታነጽባቸው ትምህርት ቤቶች ናቸው። በዚህ ይዘት ስር እስከ ዛሬ የዘለቁት ስራዎቹ አሊን እንዳንረሳው አድረገውታል፤ በሕይወት ቢለይም በኢትዮጵያ ሙዚቃ ታሪክ ሕያው ሆኖ እንዲኖር አድርገውታል። የዓሊን ሕያውነትና የሐዘን መልዕክቱን የገለጸው አርቲስት ሰርጸ ፍሬስብሐት “ዓሊ፥ የጥዑም ድምጽ ባለተሰጥዖነቱ ብቻ አልነበረም የሚያስደንቀው። ፈረንጆቹ "genius" የሚሉት ዓይነት የሙዚቃ ሰው ስለነበረም እንጂ” ብሏል። አክሎም ሙዚቃን፤ በዕውቀት ምሥጢሯን ዐውቆ የተጫወታት ታላቅ ድምጻዊ፣ ዓሊ ሞሐመድ "ብራ" ነበር ሲልም አመልክቶ ዓሊ፥ ሙዚቃዎቹን ራሱ ያቀናብራል፣ ዑድ፣ ጊታር፣ ኪቦርድ፣ ፒያኖ፣ አኮርዲዮን እና ሐርሞኒካ አሳምሮ ይጫወታል” ሲል ሁለገብነቱን መስክሯል። አሊ ከክብር ዘበኛ፣ ከአይቤክስ፣ ከኢትዮ ስታር ሙዚቀኞች ጋር በሠራቸው የሙዚቃ ሥራዎች፣ አድማጮቹ ብቻ ሳይኾኑ፣ አብረውት የሠሩት ሙዚቀኞች ኹሉ እንደተደነቁበት፣ ሙዚቃን እንዳስከበረ ዕድሜ ልኩን የኖረ ታላቅ ሙዚቀኛ ነበር። በሙዚቃ ስራዎቹ ባለ ራዕይነቱንና ህዝባዊነቱን ያስመሰከረው ዓሊ ከመለያየት ፍቅርን ከጸብ አንድነትን በሚያመለክቱ ሰራዎቹ ትምህርት ሰጥቷል። ”Barnootaa ammas Barnootaal” መማር አሁንም መማር” በሚለው ኦሮሚኛ ሙዚቃውም ዕውቀት የአድገት ብርሃን መሆኑን ከዘመናት ቀድሞ አስገንዝቧል። በኦሮሚኛ ቋንቋም ሆነ በሌሎች ቋንቋዎች በተጫወታቸው ሙዚቃዎችም ሳይሰለች የሚደመጠው አሊ በሙዚቃዎቹ በሚያስተላልፋቸው መልዕክቶች የተነሳ ያለ ቋንቋ ገደብ የብዙኃን አንደበት የሚያቀነቅነው ሁለገብ ሙያተኛ ነው። አንጋፋው አርቲስት ዓሊ ቢራ ከ260 በላይ ሙዚቃዎችን ያቀነቀነ ሲሆን ስድስት አልበሞችን በማሳተም በኢትዮጵያ የሙዚቃ ታሪክ ዘላለማዊ አሻራውን አኑሯል። ከድሬዳዋ ገንደቆሬ ተነስቶ በአለም አደባበይ በሙዚቃ ታሪክ የሰራው አሊ የኦሮሞን ባህልና ማህበረሰባዊ እሴት ከማስተዋወቅ ባለፈ የህዝብ ድምጽ ሆኖ ሰላማዊ ትግል አካሂዷል። የተቸገሩ ወገኖችን፣ ታዋቂ ግለሰቦችንና መጠጊያ የሌላቸውን ከመርዳት ፋውንዴሽን እስከ ማቋቋም የደረሰው የአሊ ህዝባዊ ልብ ዛሬም…በመረዋ ድምጹ አጠገብ እንዳለ ወዳጅ እየተናፈቀ ይደመጣል።
ደምና ወዙን የሰጠን የኢትዮጵያ አንበሳ ይነሳ ይወሳ!
Nov 3, 2022 261
ጀግንነትና ድል አድራጊነት ሲነሳ የኢትዮጵያ አርበኞች ልጅና ያለመሸነፍ ምልክት የሆነው ሠራዊታችን ወይም ወታደር በቅድሚያ ወደ ልባችን ይመጣል ። ከሠራዊቱ የጀግንነት መገለጫዎች መካከል ክተት ሰራዊት የተባለባቸውን የጦር አውድማ በድል አድራጊነት ተወጥቷል ይህም ከኢትዮጵያ ዳር ድንበሮች አልፎ በተለያዩ ሀገራት ሰላም ማስከበር በተሰማራባቸው ። ለሠራዊቱ ህልሙም፣ ሀሳቡም፣ ተልዕኮሙም የሀገሩን ሰንደቅ ከፍ ማድረግ፣ ለህዝቡ ደህንነት መረጋገጥ ሁሌም ዋጋ እየከፈለ መሆኑን ታሪክ ይመሰክራል ደሙ የፈሰሰባቸው አጥንቱ የተከሰከሰባቸው ስፍራዎችም ለትውልድ ነጻነትን በመዘከር ህያው ምስክር ሆነዋል። ሠራዊቱ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስከበር በአስቸጋሪ በረሃዎችና አጥንት በሚሰብሩ ቀዝቃዛ ስፍራዎችን ተቋቁሞ ሕይወቱን ሳይሰስት በቀበሮ ጉድጓድ ውስጥ ተዋድቋል እየተዋደቀም ነው። ለዚህም ነው ጀግናውን ወታደር የኢትዮጵያ አንበሳ ይወሳ ይነሳ የምንለው። ሞትን በሚያስናፍቁ ስፍራዎች ለሰንደቁ ከፍ ማለት ለሀገሩ ጽናት የከፈለውን ዋጋ በመዘከርና በማመስገን ጭምር። ይልቁንም ዛሬ ጥቅምት 24ን ስናስብ በተፈጸመበት ክህደት ከጀርባው የተወጋበትን ያስተናገደውን መከራ የምንዘክርበት ዕለት በመሆኑ፤ ጀግናው ወታደር ይወሳ ይነሳ የኢትዮጵያ አንበሳ እያልን የከፈለውን ዋጋ በማወደስ ከጎኑ ቆመን አለኝታነታችንን እንመሰክራለን። የተካደው ሰሜን እዝ በተሰኘው መጸሃፍ እንደተገለጸው ጥቅምት 24 2013 ዓ.ም በሠራዊቱ ላይ የተፈጸመው የክሀደትና ጭፍጨፋ ተግባር የውጭ ጠላቶችስ ከዚህ የከፋ ምን ይፈጽማሉ እንድንል የሚያደርግና ባንዳነት የት ድረስ እንደሚጓዝ የሚያሳይ ክስተት ነው። ከጥቃቱ ቀደም ብሎ የትግራይ ክልልን ጨምሮ በኢትዮጵያ የተለያዩ ስፍራዎች የአንበጣ መንጋ ተከስቶ ስለነበር ሰራዊቱ ባለበት ስፍራ ዳር ድንበርን ከማስከበር ጎን ለጎን አንበጣውን ለመከላከል ሲረባረብ ነበር። ሠራዊቱ ከደሞዙ ቀንሶ የህክምና ተቋማትን፣ ትምህርት ቤቶችን፣ እንዲሁም ሌሎች አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን በመገንባት ህዝባዊነቱን አሳይቷል። ደሙንና ወዙን በሰጠ ጀግና ላይ ነው ታዲያ “መብረቃዊ” በተባለው ጥቃት ዘግናኝ በደል ጥቅምት 24 ቀን 2013 የደረሰበት። ወታደሩ ወገን አለኝ መከታ አለኝ ሲል በቀበሮ ጉድጓድ ከ20 ዓመታት በላይ ዋጋ በከፈለበት ስፍራም ነው ከጀርባው የተወጋው፤ ጥቃቱ አንኳን በሀገር ሰራዊት ላይ ሊፈጸም ቀርቶ በጠላት ላይ እንኳን ይደረጋል የማይባል ነበር። ጀግናው ሠራዊት የተቃጣበትን ጥቃት በመመከት የጓዶቹን ደም በአሸናፊነት ተበቅሏል የአባቶቹን ደማቅ ታሪክም በደሙ ጽፏል። በቀኝ ግዛት ዘመን የነበረውን የባንዳነት ተግባር ያሸነፉ አርበኞች ልጅ የሆነው የኢትዮጵያ ወታደር በዚህ ዘመንም የጀግና ልጅ ጀግና መሆኑን አስመስክሯል። ያለ ልዩነት ለሀገሩ ክብር ዋጋ የሚከፍለውን የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት “ጀግናው ወታደር ይወሳ ይነሳ የኢትዮጵያ አንበሳ” እያለን ከጎኑ ቆመን መደገፍ ኢትዮጵያዊ ግዴታችን ነው።
የውጭ ባንኮች መግባት ...
Oct 14, 2022 344
በኢትዮጵያ በ1901 ዓ.ም የባንክ አገልግሎት መጀመሩን መረጃዎች ያመለክታሉ። ከኢትዮጵያ ባንኮች በተጨማሪ የውጭ ባንኮች እ.አ.አ እስከ 1970ዎቹ ድረስ በአገር ውስጥ ይንቀሳቀሱ እንደነበር መረጃዎች ያስረዳሉ። በኢትዮጵያ ስር ነቀል ለውጥ ተካሂዶ ደርግ ሥልጣን ከያዘ በኋላ የውጭ አገር ዜጎች ባንኮች ዘግተው ወደ አገራቸው ተመልሰዋል። አገሪቷ ከምትከተለው የሶሻሊዝም ርዕዮተ ዓለም የተነሳ የውጭ ባንኮች ሙሉ በሙሉ ጠፍተዋል። ይህ ሂደት በኢህአዴግ መንግስትም ቀጥሏል። የኢኮኖሚ ባለሙያና አማካሪ አቶ ዘመዴነህ ንጋቱ እንደሚገልጹት ከ1991 ዓ.ም ጀምሮ በኢትዮጵያ ባንክ ለመመስረት ኢትዮጵያዊ ዜግነት ሊኖረው እንደሚገባ በህግ ተደነገገ። ባለሙያው ከኢትዮ-ቢዝነስ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ መንግሥት የውጭ አገሮች ባንኮች በኢትዮጵያ የባንክ ዘርፍ ውስጥ ገብተው መሥራት እንዲችሉ የሚፈቅድ ፖሊሲ ተግባራዊ እንዲሆን ተፈቀዷል። በዚህ ስርዓት “ባንኮች መግባታቸው የጎላ ፋይዳ ይኖረዋል” ብለዋል። የውጭ አገሮች ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ መግባት አገሪቷ በምሥራቅ አፍሪካ ትልቅ ኢኮኖሚያዊ አቅም እንዲኖራትና ተፅዕኖ ፈጣሪነቷን ለማሳደግ እንደሚያስችላል ተስፋ ያደርጋሉ። የዘርፉ ባለሙያዎች እንደሚናገሩት ከሆነ የውጭ አገር ባንኮች ወደ አገር ውስጥ ከገቡ የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ችግር ለመፍታት፣ በአነስተኛ ወለድ ብድር ለማግኘትና ከግማሽ ምዕተ ዓመት በላይ በተለምዶ ሲሠራበት የነበረው የባንክና የመድን አገልግሎቶች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን ጠብቀው እንዲሠሩ ጭምር ትልቅ ዕገዛ ሊያደርግ ይችላል። በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ጨምሮ ከ20 በላይ ባንኮች ይገኛሉ። እነዚህ ባንኮች በቁጥር ደረጃ ከፍተኛ ይሁኑ እንጂ በካፒታል አቅማቸውና በአደረጃጀታቸው በዓለም ዓቀፍ መለኪያ ዝቅተኛ ስለመሆናቸው ነው የኢኮኖሚ ባለሙያው አቶ ዘመዴነህ የሚያመለክቱት። እንደርሳቸው ገለጻ፤ ከሰሃራ በታች ከደቡብ አፍሪካና ናይጄሪያ ቀጥሎ ሦስተኛው ትልቁ ኢኮኖሚ የሚባለው የኢትዮጵያ ነው። የኢትዮጵያ ባንኮች ግን በኢኮኖሚው ደረጃ ልክ ያደጉ አይደሉም። ይህም የኢኮኖሚ እድገት ግቡን በእነዚህ የግል ባንኮች ብቻ ማሳካት አይችልም። ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ውጭ በተጨማሪ እነዚህ በአገር ውስጥ የሚገኙ የግል ባንኮች ጠቅላላ ሀብታቸው ቀላል እንዳልሆነ የገለጹት ባለሙያው፤ ኢትዮጵያ እንድታድግ ከተፈለገና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ለመሳብ የውጭ ባንኮች መግባት አስፈላጊ ነው። የውጭ ባንኮች ወደ አገር ውስጥ ሲገቡ ግን ቀድሞ በተሰራ ህግና ስርዓት መበጀት ይኖርበታል። በአፍሪካም እንደ ደቡብ አፍሪካ እና ናይጄሪያ ያሉ አገሮች የውጭ ባንኮችን ወደ አገራቸው በማስገባት አገራዊ ኢኮኖሚያቸውን ማነቃቃት ችለዋል። “በዘርፉ ከተሰማሩ ባንኮች ውጭ የውጭ ባንኮች ሲገቡ ከአገር ውስጥ ባንኮች ጋር በሽርክና መንገድ ቢገቡ ተመራጭ ይሆናል” ሲሉም ነው ያስረዱት። በዚህም የገንዘብ አቅም ማሳደግና የእውቀት ሽግግር ማድረግ ለሚችሉ ባንኮች ቅድሚያ ቢሰጣቸው ተመራጭ እንደሚሆን ነው ያመለከቱት። የኢኮኖሚ ባለሙያው አቶ ዘመዴነህ አጽነኦት ሰጥተው እንደገለጹት፤ የውጭ ባንኮች በአገር ውስጥ መግባት በፋይናንሱ ዘርፍ የሚታየውን የስራ ባህልና አስተሳሰብ በማምጣት በንግዱ ዓለም ላይ የጎላ ሚና ይኖረዋል። እስካሁን ከአፍሪካ ውጭ ያሉ ባንኮች ምንም ፍላጎት ባያሳዩም እንደ ደቡብ አፍሪካና የናይጄሪያ እና የኬንያ ባንኮች ፍላጎት አሳይተዋል። በዚህም እንደ አገር የሚመጡትን ታሳቢ በማድረግ የመተዳደሪያ ህጎችን አዘጋጅቶ መጠበቅ ይገባል። በሌላ በኩል የአገር ውስጥ ባንኮችን በማጠናከር ጠንካራ ባንክ እንዲሆኑ ለማስቻል በቁጥር ብዙ የሆኑትን ወደ ትንሽ ቁጥር ሰብሰብ ብለው የተሻለ አስተዳደራዊና ካፒታላዊ አቅም መፍጠር ይገባል። ኢኮኖሚስቱ የአፍሪካ ቻምበር ኦፍ ኮሜርስ ፕሬዝዳንት አቶ ክቡር ገና በበኩላቸው እንደሚሉት፤ የባለሙያዎችና ከዘርፉ እንዲሁም ከማህበረሰቡ የተውጣጡ ግለሰቦች ዘንድ ውይይት መደረግ ይገባዋል። ውይይቱ እነማን ባንኮች ይመጣሉ? ምን የተሻለ ነገርስ ይዘው ይገኛሉና ምን መደረግ አለበት? የሚለውን መመለስ ይችላል። “እነዚህ ባንኮች ሲገቡ የውጭ ምንዛሬ ችግርን ከሚቀርፉት በላይ ትልልቅ አገራዊ የልማት ድርጅቶች ብድሮችን በማበደር ሀብት ማሰባሰብና ንግድ ባንክን ጨምሮ ሌሎች የአገር ውስጥ ባንኮችን ያቀጭጫል” ሲሉም ይሞግታሉ። ለዚህም የውጪ ባንኮች ይግቡ ሲባል ከብሄራዊ ባንክ በተጨማሪ ሌሎች ገለልተኛ የፋይናንስ ዘርፍ ተቆጣጣሪ ኤጀንሲዎች መቋቋም ግድ ሊሆን እንደሚችል የተናገሩት ደግሞ የኢኮኖሚ ባለሙያው አቶ አሰግድ ገብረመድን ናቸው። በዓለም ዓቀፍ የፋይናንስ ደረጃ የሰለጠነ በዘርፉ ያላቸውን ልምድ ሊያሳድጉ እንደሚገባም ነው የጠቆሙት። “ፋይናንስ ዘርፉን የሚደግፍ እና በርካታ ማሠልጠኛ ተቋማት አለመኖራቸው የፈጠረው ክፍተት ቀላል ባለመሆኑ በዚህ ላይ ብዙ መስራት ይጠይቃል” ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ በቻርተር ባንክ ደረጃ የበቃ የፋይናንስ ዘርፍ ባለሙያ ውስን በመሆኑ ችግር ሊሆን እንደሚችል አስረድተዋል፡፡ አሁን ባለው ደረጃ የኢትዮጵያ ባንኮች ከዓለም የግብይት ቋንቋ ሥርዓት ጋር ራሳቸውን፣ ሠራተኞቻቸውን እያበቁ አይደለም። ስለሆነም “የውጭ ባንኮች ሲገቡ ሊፈተኑበት ይችለሉ” ብለው እንደሚያምኑ ነው አቶ አሰግድ የሚገልጹት፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን “የሥራ መሪዎችንም ሊመለከት ይችላል” የሚል ሥጋትም አላቸው፡፡ ይህም ቢሆን ግን አሁን ባለው አቅም በውህደትና በጥምረት የአገሪቷን ባንኮች ብቁ ሊያደርጉ የሚችሉ ዕድሎች ስላሉ በዚህ መጠቀሙ ተመራጭ እንደሚሆን መክረዋል። ባለሙያዎቹ እንደሚያመለክቱት፤ የአገር ውስጥ ባንኮች በብዛት ያገለግሉ የነበረው ከፍተኛ የንግድ ተቋማትንና ግለሰቦችን ነው። መካከለኛ እና ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን የማህበረሰብ ክፍሎች ታሳቢ ያደረገ አገልግሎት ለመስጠት የውጭ ባንክችን የማስገባት ውሳኔ ተጨማሪ ተወዳዳሪ ስለሚሆኑባቸው ይህንን መካከለኛ እና ዝቅተኛ ኢኮኖሚ ያለውን ማህበረሰብ ዋነኛ ደንበኞቻቸው አድርገው ሊመጡ ቢችሉ መልካም ስለመሆኑ ያስረዳሉ። በኢትዮጵያ “የባንክና ፋይናንስ ተቋማት አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ሆነው ለመቀጠል አዲስ አሰራር መከተል ይገባቸዋል” ያሉት ደግም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ንግድ ስራ ኮሌጅ የአካውንቲንግና ፋይናንስ ትምህርት ክፍል ሃላፊ ዶክተር ዳኪቶ አለሙ ናቸው። ዶክተር ዳኪቶ አለሙ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ ግሎባላይዜሽን በተስፋፋበት ሁኔታ የፋይናንስ ስርዓቱን በር ዘግቶ በመቀመጥ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ መሆን አይቻልም። ኢትዮጵያ የባንክ ዘርፉን ለውጭ ባንኮች ክፍት ለማድረግ ማቀዷ ተገቢነት አለው። በአገር ውስጥ ባንኮች ብቻ ግዙፍ ምጣኔ ሃብት መገንባት እንደማይቻል ደቡብ አፍሪካን ጨምሮ ሌሎች አገሮች ለውጭ ባንኮች በራቸውን ክፍት ያደረጉ የአፍሪካ አገሮች በኢንቨስትመንት ፍሰትና ሌሎች ዘርፎች ተጠቃሚ ስልመሆናቸውም ያስርዳሉ። የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ከካፒታል ገበያ፣ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት እና የውጭ ምንዛሪ ከማስገኘቱም በላይ ባንኮች ይዘውት የሚመጡትን ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የአገር ውስጥ ባንኮችም ማግኘት ከቻሉ ተወዳዳሪ ከመሆን ባለፈ የተሻለ እድገት የማስመዝገብ እድላቸው ሰፊ ስለመሆኑ አያጠራጥርም። ኢትዮጵያ በቀጣይ ለምትገነባው ግዙፍ ኢኮኖሚ የባንክ ዘርፉን ማጠናከር ወሳኝ ነው። ይህ ለውጭ አገሮች ክፍት ለማድረግ የተፈቀደው ፖሊሲ በቂ የዝግጅት ጊዜ መስጠት፣ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር መምከር፣ የውጪዎቹ የሚገቡበት መንገድ በህግ ማዕቀፍ ውስጥ የሚካተትበት መመሪያ ማውጣት ትኩረት የሚሻው ጉዳይ ነው።
መስቀል ደመራ - የመስከረም ደማቅ መልክ ማሳያ
Sep 26, 2022 327
(አየለ ያረጋል) መስከረም ሁለንተናዊ ውበቱ ድንቅ ነው፤ ትዕምርቱም ጉልህ ነው፤ የወራት ቁንጮው መስከረም ደማቅ መልኮች መካከል አንዱ ደመራ፤ በዓለ መስቀል ነው። ከደመራው ዓመድ ልጆች ግንባራቸው ላይ የመስቀል ምልክት በማድረግ የዛሬ ዓመት አድርሰኝ ስለት ይሳላሉ። መስቀል የወል ክብረ በዓል ነው፤ የጋርዮሽ አከባብር። በዚህ ዕለት የግድ በዓሉን በጋራ ማክበር ስለሚያስፈልግ የተጣላ ጎረቤት ሁሉ ይታረቃል። በኢትዮጵያ ዘመን ቆጠራ ቀለበት ውስጥ ወርኅ መስከረም ተናፋቂ ነው። ሊቃውንት መስከረምን ሲፈትቱት መስ- 'ዐለፈ፤ ከረመ' ይሉትና 'ክረምቱን ማስከረሚያ፤ የጥቢ መባቻ" ወርኅ ሲሉ ያመሰጥሩታል። ደራሲ ካህሳይ ገብረ እግዚአብሔር “ቀዳማይ፣ ርዕሰ ክራሞት፣ መቅድመ አውርኅ፣ ርዕሰ ዐውደ ዓመት፣ የክረምት ጫፍ መካተቻ፣ የመፀው መባቻ” ይሉታል ወርኃ መስከረምን። እናም ዘመነ ማዕዶቷን፤ ወርኅ ተውሳኳን ‘ጳጉሜን’ ተሻግሮ መስከረምን መሳም ይጓ'ጓ'ል። የመስከረም ጥባት በአያሌው ይሻታል። መስከረም የወራት ሁሉ ቁንጮ ይመስላል። መስከረም ዘመን ያስረጃል፤ አዲስ ሕይወትና ተስፋ ደግሞ ይደግሳል። የባህር ሐሳብ ሊቃውንት መስከረም 1 ቀን ዓለም የተፈጠረበት፤ ኖኅ ከጥፋት ውኃ በኋላ ውሃው መጉደሉን ለማረጋገጥ ወደ ምድር የላካት እርግብ ቅጠል ይዛ የተመለሰችበት፣ እስራኤላዊያን ከግብጽ ባርነት ሲወጡ ቀይ ባሕርን የተሻገሩበት የብስራት ዕለት እንደሆነ ያነሳሉ። በእነዚህና ሌሎች ኃይማኖታዊ ትውፊቶች ከጥንት ጀምሮ ነው መስከረም ለዘመን መለወጫነት የተመረጠው' ይላሉ። ዕለቱም ‘ርዕሰ ዓውደ ዓመት’ ይሉታል። መስከረም ለመልክዓ ምድሩ፣ ለሰውና ለእንስሳት ሁሉ ‘ፍስኃ ወተድላ’ በማለት የደስታና የተድላ ወር ነው። በመስከረም ምድር ትረጋለች፣ በአበቦች ታጌጣለች፣ በእንቁጣጣሽ ትፈካለች። ውኆች ይጠራሉ። በሰማዩ ላይ ሰማያዊ ብርሃን ይወጣል፤ የጥቁር ደመና ጋቢ ይገፈፋል፤ ክዋክብት በሰማይ ብረት ምጣድ ላይ መፈንጨት ይጀምራሉ። ዕጽዋትና አዝዕርት እንቡጦች ይፈነዳሉ። የመብረቅ ነጎድጓድ ተወግዶ የሰላምና የሲሳይ ዝናብ ይዘንባል። እንስሳት የጠራ ውሃ እየጠጡ፣ ለምለም ሳር እየነቸረፉ ይቦርቃሉ። እርሻ የከረሙ በሬዎች፣ ጭነት የከረሙ አህዮች መስከረም አንጻራዊ የእፎይታ ወርኃቸው ነው። ነጎድጓድ በአዕዋፋት ዝማሬ ይተካል። ንቦች አበባ ይቀስማሉ፤ ቀፏቸውን ያደራሉ። ቢራቢሮ ሳትቀር ‘በመስከረም ብራ ከኔ በላይ ላሳር’ ብላ ትከንፋለች። ለሰው ልጆች የመስከረም ደጅ ሲከፈት ግብዣው የትየለሌ ነው። ምድር ብቻ አይደለችም በ’እንቁጣጣሽ’ የምትዋበው። መስከረም ለሰው ልጆችም በተለይም ለወጣቶች የፍቅር፣ የእሸትና የአበባ ወር ነው። የሰላም፣ የንጹህ አየር፣ የጤና ድባብ ያረብብበታል። የጋመ በቆሎ እሸት ጥብስ፤ ቅቤ ልውስ፤ ቅቤ በረካ፤ መስቀል፣ ደመራ ይናፈቃል። የተጥፋፋ ይገናኛል። ‘ሰኔ መጣና ነጣጠለን’ ብለው ወርኃ ሰኔን የረገሙ ተማሪዎች ተናፋቂያቸውን ያገኛሉና ‘መስከረም ለምለም’ ብለው ያሞካሹታል። የገበሬው የሰብል ቡቃያ ያብባል፣ እሸት ያሽታል። ጉዝጓዝ ሣር፤ ትኩስ ቡና ይሸታል። 'መስከረም ሲጠባ ወደ አገሬ ልግባ …’ እንዲሉ የተሰደዱት በአዲስ ዓመት መባቻ የአገራቸውን አፈር ያማትራሉ። ’ኢዮሃ አበባዬ፤ መስከረም ጠባዬ’ የሚሉ ሕጻናት ተስፋና ምኞታቸውን በወረቀት ያቀልማሉ፤ የአበባ ስዕላት ይዘው በየደጃፉ ይሯሯጣሉ፣ የ’ዕደጉ’ ምርቃት ያገኛሉ፤ በደስታ ይንቦጫረቃሉ። በዚህ ድባብ ነው እንግዲ መስከረምን የግዑዛንም የሕይወታውያንም የነፃነት፣ የተስፋና የፍቅር ወርኅ ተደርጎ የሚናፈቀው። በጥቅሉ የባለ13 ወር ፀጋዋ ኢትዮጵያ መስከረም ሁለንተናዊ ውበቱ ድንቅ ነው። ትዕምርቱም ጉልህ ነው። ለብዙ ሺህ ዘመናት ባለታሪኳ ኢትዮጵያ በስልጣኔ ወደኋላ እየተሳበች ወደ ድህነት ከርመት ከገባች ክፍለ ዘመናት ተቆጥሯል። ተፈጥራዊ አዱኛ ሳይርቃት በእርስ በርስ ጦርነት፣ በጠላት ፍላጻዎች ብዛት፣ በድንቁርና... የተነሳ ሰንኮፎቿ አልተነቀሉላትም። ዛሬም በብዙ ምስቅልቅሎሽ ውስጥ በመሆኗ ይህን ወርኅ መስከረም በሙሉ ሰላም ማክበር አልቻለችም። ደመራ እና መስቀል የወራት ቁንጮው መስከረም ደማቅ መልኮች መካከል አንዱ ደመራ፤ በዓለ መስቀል ነው። የዕንቁጣጣሽ ተከታይ ብሔራዊ በዓል ነው -መስቀል። መስቀልና ኢትዮጵያ ታሪካዊ ትስስራቸው ጥብቅ ነው። መስቀል ከመንፈሳዊ አንድምታው ባሻገር ባህላዊ ትውፊቱ በቀላሉ አይገለጽም። እንደ ኃይማኖተ አበው ሀተታ መስቀል ኢየሱስ ክርስቶስ ዓለምን ለማዳን፣ ለፍጡር የሰው ልጆች ያለውን ጥልቅ ፍቅር የገለጸበት ዓርማ ነው። በዚህም መስቀልን አማኝ ምዕመናንና ካህናት የድህነትና የእምነት ምልክታቸው፤ የርኩስ መንፈስ ማባረሪያ መሳሪያቸው አድርገው ብቻ አይደለም የሚመለከቱት። ነገረ መስቀሉ እምነቱ፣ ባህሉ፣ ትውፊቱ ብዙ ነው። በርካታ ኢትዮጵያዊያን መስቀል ወራሪዎችን ድል የነሱበት፣ የጠላት ሴራ ያከሸፉበት፣ ጨለማን በብርሃን የለወጡበት የታሪካቸውና ባሕላቸው የተጋድሎ ምልክት አድርገው ይወስዱታል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን መስከረም 10 ቀን ‘ተቀጸል ጽጌ’ በሚል የክርስቶት መስቀል ግማድ (ቀኝ እጁ ያረፈበት ክፋይ) ከኢየሩሳሌም ተነስቶ ኢትዮጵያ የገባበትን ቀን ታከብረዋለች፤ መስከረም 17 ቀን ደግሞ መስቀሉ የተገኘበትን። መስከረም 17 ቀን የሚከበረው በዓለ መስቀል ከኃይማኖታዊ አስተምህሮው ባለፈ ባህላዊ ትውፊትነቱ የጎላ በመሆኑ በአብዛኛው ኢትዮጵያዊያን ዘንድ ይናፈቃል። የመስቀል ክብረ በዓል መለያው ደመራው ነው። የደመራ አደማመርና ማብራት ስነ ስርዓት በሁሉም የኢትዮጰያ አካባቢዎች ተመሳሳይ እንዳልሆነ ደራሲ ካህሳይ ገብረ እግዚአብሄር ይተርካሉ። በትግራይ፣ በጎንደር፣ በወሎ፣ በዋግኸምራ፣ በአዊና በከፊል ጎጃም ደመራ ማታ ላይ ተደምሮ ንጋት ላይ ይለኮሳል። በከፊል ጎጃም፣ በሸዋ፣ በአዲስ አበባ፣ በጉራጌ፣ በጋሞ፣ በወላይታና ሌሎች የደቡብ ኢትዮጵያ አካባቢዎች ደግሞ እንደየ አካባቢው ተለምዶ መስከረም 16 ከዕኩለ ቀን ጀምሮ እስከ አመሻሽ ድረስ ደመራው ይለኮሳል። መስቀል እንደየአካባቢውና ባህሉ የሚናፈቅበት ዕልፍ ገጽታዎች አሉት። ለምሳሌ በእኔ ገጠራማ ትውልድ ቀዬ በወፍ በረር ስገልጸው፤ በቅድመ ደመራ ሰሞን ተራራ ለተራራ፣ ወንዝ ለወንዝ፣ ቋጥኝ ለቋጥኝ በልጅነት ወኔና ስስት እንኳትናለን፤ የደመራ ግንድ፣ አደይ አበባ፣ የደቦት ደረቅ እንጨት ለመልቀም። መስከረም 16 አመሻሽ ከብቶች በጊዜ ከተሰበሰቡ፣ ወደ ግርግም ከገቡ፣ የመስከረም 16 መዓልት ለፅልመት ሲረታ የመንደሩ ወጣቶች ወደ ተለመደችዋ ‘አፋፍ’ እንሰባሰባለን-አፋፏ ለደመራ ትመረጣለችና። ከአጎራባች መንደሮች የተሻለ ደመራ ለመደመር እንጥራለን። እስከ ምሽቱ 2 ሰዓት በጨለማ ደመራችንን ደምረን፣ የደመርነውን ደመራ እንቧለሌ ዞረን፣ ባርከንና መርቀን፣ ጨፍረን ወደየ ቤታችን እንበታተናለን፤ ከሰዓታት በኋላ ለመገናኘት ደግሞ እንነፋፈቃለን። የመስከረም 16 አዳር እንቅልፍ ይነሳል። በሌሊት ተነስቶ፣ ችቦ አብርቶ፣ ‘እዮሃ ደመራ’ እያሉ ወደ ደመራው ስፍራ ለመሄድ፣ ደርሶም ደመራውን ከሌሎች አጎራባች የመንደር ደመራዎች ቀድሞ ለመለኮስ ጉጉቱ የትየሌሌ ነው። አጠባብ ላይ ከቤት ያለ ጉብል ሁሉ (ልጃገረዶችና ወንዶች) ወደ ደመራ ያመራሉ። ከምድጃ አልያም ከክብሪት እሳት ጭሮ ደቦቱን (ችቦውን) ይለኩሳል። ደቦቱ በእሳት ከተያያዘ በኋላ ወላጆቹን፣ ከብቶቹን፣ የጓሮ አትክልቱን፣ በደጃፍ ያሉ ሕይወታዊያንን በሙሉ “እንጎረጎባህ፤ እንጎረጎባችሁ” ይላል። ተጠያቂውም “ዓመት ዓመቱን ያድርስህ” ማለት ይጠበቅበታል። ለብሽሽቅ ከሆነ ደግሞ “ወስፋት ይላጥህ'” ማለቱ አይቀርም ይሄኔ በተቀጣጠለ ችቦ አጸፋውን የመስጠት ልምድ አለ። ከቤት ተነስተን ደመራው ከተደመረበት አፋፍ እስከምንደርስ በአንድ እጃችን መጠባበቂያ ደቦት፣ በሌላው ያቀጣጠልነውን ችቦ ይዘን የደመራ ግጥሞችን እየደረደርን እንቀጥላለን። የመስከረም እኩሌታ ውብ ማሳ ከየቤቱ ከሚወጡ የችቦ እሳት ነበልባል ብርሃን ይታጀባል። ከሚዘወተሩ ስንኞች መካከልም፡- እዮሃ አበባዬ መስከረም ጠባዬ… እዮሃ አረሬ አረሬ መስቀል ጠባ ዛሬ በሸዋ በትግሬ… ይጠቀሳሉ። ከደመራው ስፍራ ስንደርስ የ’እንጎረጎባህ! እንጎረጎባሽ! እንጎረጎባችሁ’ ድምጾች ይበረታሉ። ሁሉም ልጆች እስኪሰባሰቡ መልካምም ሆነ እኩይ የአጸፋ መልሶች እየተመለሱ ጥቂት ይቆያል። ደመራውን ሶስት ጊዜ ‘እዮሃ አበባዬ፣ መሰከረም ጠባዬ” እና ሌሎች የራስን ደመራ የሚያሞካሹ፣ የሌሎቹን የሚነቅፉ፣ ዘመኑ የጥጋብ ዘመን እንዲሆንና እንዲባረክ የሚመኙ ስንኞች እየተገጠሙ እንቧለሌ እንዞረዋለን። በስፍራው በዕደሜ ታላቅ የሆነ ሰው ለችቦ ማስገቢያ ክፍት በተተወው የደመራው ገጽ በኩል የተለኮሰ ደቦቱን ያስገባል። ሌላው ሁሉ እሱን ተከትሉ ወደ ደመራው ደቦቱን ይጨምራል። ደመራው መቀጣጠል ይጀምራል፣ ጭሱም ይጨሳል፣ የእሳቱ ነበልባል ከመስከረም የንጋት ውርጭና ብርድ ይገላግላል። ደመራውን ዙሪያውን ተኮልኩለን ወሬ፣ ሀሜት፣ መበሻሸቅ፣ ባለፉት ክረምት ወራት ስለነበሩ የተሳታፊዎች ገጠመኞች በአያሌው እንሰልቃለን። የተጣላም ሳይቀር ታርቆ ያወራል፣ በዛ መበሻሸቅም አልፎ አልፎ የሚጣላ ቡጢ የሚሰናዘርም አይጠፋም። በዚህ መልክ የደመራው አምድ (ምሰሶ) እስክትወድቅ፣ ሌሊቱ የአህያ ሆድ እስኪመስል እናነጋለን። ምሰሶው ወደዬት እንደሚወደቅ ለማየት እንጓጓለን። ወደ ምሥራቅ ከወደቀ የጥጋብ ዓመት፤ ወደ ምዕራብ ከሆነ ግን የችጋር ዓመት ተደርጎ ይገመታል። ምሰሶው ከወደቀ በኋላ ሌላ ትዕይንት ይከተላል። እንጨት ካለቀ በአካባቢው ከሚገኝ የግለሰብም ሆነ የወል ንብረት እንጨት በመስረቅ ከደመራው ላይ ይጨመራል። በቀያችን የመስቀል አንዱ ባህሉ የቦቆሎ እሸት ናፍቆት ነው። ቦቆሎ ቢያሽትም ባያሽትም፣ ከማሳው ተዘንጥፎ በይፋ በሰፈሩ የሚቀመሰው የመስቀል ዕለት ነው። እናም በሌሊት ተቧድነን በሚያመች ቦታና ማሳ በመግባት ቦቆሎ የመስረቅ ልማድ አለ። ባለቦቆሎውም ከነገ በኋላ ቢሰማም ዓመታዊ ደንብ ስለሆነ ቦቆሎ ማሳዬ ተጎዳብኝ ብሎ አይቆጣም። በደመራው ፍም ጠብሰን እሸቱን እንበላለን። ከደመራው ዓመድ በግንባራችን ላይ የመስቀል ምልክት እናደርጋለን። የዛሬ ዓመት አድርሰኝ ስለት እንሳላለን። አሁን ሰማዩ የአህያ ሆድ መስሏል። ቀጣዩ ተግባራችን በደቦ ወደ መንደር መዞር ነው። ቀሪ ችቧችንን አቀጣጥለን እንደ ዕድር በአንድ ደመራ አባል በሆኑ ቤቶች ሁሉ እየዞርን ‘እንጎረጎባችሁ’ እንላለን። እንደ ከተማ ልጅ ሳንቲም አይደለም የሚሰጠው። ለዚያ ብለን ባዘጋጀናት ሳህን፣ ጣሳ ወይም ሌላ መያዣ ዱቄት እንለምናለን። የበሬና የላም ስም እየጠራን፤ እንገጥማለን። ሁሉን ቤተሰብ ካዳረስን በኋላ የሰበሰብነውን ዱቄት ‘ዓመት ዓመቱን ያድርሳችሁ’ ከሚል ምርቃት ጋር ተሸክመን ወደ ደመራው ስፍራ እንመለሳለን። ከዛው የደመራው ጉባኤ ወስኖ ለተመረጠች ሴት ዱቄቱ ይሰጣል። አነባበሮ እንድትጋግር በወጣቶች ዘንድ ቀጭን እመቤት (ባለሙያነቷ የተመሰከረላት) ይሰጣል። የማገዶ እንጨትም ተለቅሞ ይሰጣታል። ተመራጯ ሴት ባለትዳር ብትሆንም ባትሆንም ዳቦ ጋግራ ለአመሻሽ ለማድረስ አደራዋን ትረከባለች። የመስቀል ዕለት በጎች ታርደው፣ ጠላ ቀርቦ፣ ሰፈርተኛው ተሰባስቦ ሲጫውት ይውላል። መስቀል የወል ክብረ በዓል ነው፤ የጋርዮሽ አከባብር። በተለይም ከሰዓት ለአንዳንድ ስራ ራቅ ካለ ቦታ የሄደ ሁሉ ይሰባሰባል። አመሻሽ ላይም እንደደመራው ምሽት ዕለት ሰው ይሰባሰባል። በዚህ ዕለት የግድ በጋራ በዓሉን ማክበር ስለሚያስፈልግ የተጣላ ጎረቤት ሁሉ ይታረቃል፤ ያለፈው የክረምት ጨለማ ጊዜያት ክፉ ደግ ጉዳዮች ይወራሉ። ልጆች ይቦርቃሉ። የጠዋት አደራ ተቀባይ ሴት የጋገረችውን አነባብሮ (መክፈልትም ይባላል) ታቀርባለች። እነዚህ ከመስቀል ጥቂት የአንድ ቀዬ ገጽታዎች መካከል ናቸው። እናም መስቀል ከእንቁጣጣሽ በበለጠ መልኩ በኛ መንደር ይናፈቃል። ሁሉም እንደየ አካባው ትውፊትና ወጉ ይህን ዓመታዊ ሁነት ይናፍቃል…. መስቀል በአንዳንድ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ርዕሰ ዓውደ ዓመት ይመስላል። በደቡብ ኢትዮጵያ መስቀል ከኅይማኖታዊ ይዘቱ ባህላዊ ጎኑ ይጎላል። ጉራጌዎች፣ ጋሞዎችና ሌሎችም መስቀልን ከሁሉም በዓላት የበለጠ ይናፍቁታል። የተራራቁ ቤተሰቦች የሚገናኙበት የፍቅር፣ የደስታና የእርቅ በዓል ነው-መስቀል። በጋሞ ብሔረሰብ ባሕል በዋዜማው ሰው ቢሞት አንኳን በሌሊት ተወስዶ ይቀበራል እንጂ ለቅሶ እንደማይለቀስ ይነገራል፤ ለሰው ብቻ ሳይሆን ለእንስሳቱም ልዩ መኖ እንደሚቀርብላቸው ይነገራል። ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ እንደሚባለው በጋሞዎች ደግሞ ‘ለመስቀል ያልሆነ ዱንጉዛ ይበጣጠስ’ በሚመሰል መልኩ የባህል ልብስ አለባበስ እንደሚዘወተር መምህር ካህሳይ (በህብረ ብዕር ድርሰታቸው) ጽፈዋል። መስቀል በጉራጌዎች ዘንድ አውራው በዓል ነው። ለቀጣዩ መስቀል ዝግጅት የሚጀመረው የአሁኑ ባለፈ ማግስት ነው። ሁሉም የየራሱን ዝግጅት ያደርጋል አባወራ ሰንጋ ለመግዛት፣ እማወራ ማጣፈጫውን ለማዘጋጀት፣ ወጣቶች ደመራና ደቦት ለማዘጋጀት፣ ልጆች ምርቃት ለመቀበል የየራሳቸውን ዝግጅት ያደርጋሉ። መስቀል ቤተሰብ ወዳጅ ዘመድ የሚጠያየቅበት፣ ለትዳር የደረሱ ሚስት የሚያጩበትና የሚመርጡበት ጥላቻና ቂም በፍቅርና በይቅርታ የሚታደስበት ነው። ይህም በመሆኑ በጉራጌዎች ዘንድ መስቀል ትልቅ ቦታ የሚቸረው ዓውራ ብሔራዊ በዓል ነው። ደመራ ዛሬ አመሻሽ ጀምሮ ይከበራል። ደመራ ‘ደመረ፣ ተሰባሰበ’ ከሚለው ስርዎ ቃል መጣ እንዲሉ ሊቃውንት በኃይማኖት አባቶች ይገልጻሉ። ደመራ በከተሞች ደማቅ ነው። በዓለ መስቀል ግን በአብዛኛው የጋርዮሽ ሳይሆን የተናጠል አከባብር ይስተዋልበታል። በዓለም የማይዳሰስ ወካይ ቅርስነት የተመዘገበው መስቀል በአዲስ አበባ የደመራ በዓል በብሔራዊ ደረጃ በ’መስቀል አደባባይ’ ይከበራል። የመንግስትና ኃይማኖት ተቋማት መሪዎች፤ የውጭ አገር ጎብኝዎች ይደመሙበታል። ጎረቤታሞች፣ የሩቅ የቅርብ ዘመዳሞች ተደምረው የጋራ ችቦ የሚለኩሱበት ዕለት ነው። ደመራና መስቀል የአንድነት፣ የፍቅር፣ የይቅርታ፣ አብሮነት፣ የምስጋና፣ የተስፋ… እሴቶች የሚገለጹበት ባህላዊና ኃይማኖታዊ ከብረ በዓል ነው። አገሬው ያላባሩ ፖለቲካዊ ቁርሾዎች እና ያላባሩ ግጭቶች እንዲረግቡ፣ ቂምና ጥላቻ እንዲወገድ፣ ጆሮ ቸር ወሬ እንዲሰማ፣ የአንድነት ዘመን እንዲሆን ያለውን ብሩሕ ተስፋ በየዓመቱ ይመኛል፤ ዘንድሮም። በኅይማኖታዊ አንድምታው አዳም ዕፀ በለስ በልቶ ሞትን አስከተለ። እየሱስ ክርስቶስ ደግሞ ስለሰው ልጆች መስቀል ተሸክሞ ሞትን ገደለ። መስቀሉ የብሉይ ኪዳን ሙታን እና የአዲስ ኪዳን ሕያዋንን በፍስሃ ተነስተውበታል። ከቀራኒዮ ተራራ ጫፍ ላይ ክርስቶስን የሰቀሉበትን ሰባት ክንድ ቁመት ያለው መስቀል፤ ከስቅለት በኋላ አልባሌ ቦታ ላይ አርቀው ቆፍረው ቀብረውታል። ዳሩ ሰው ዕውነትን ምን ያህል በጥልቀት ምሶ ቢቀብረው፤ አንድ ቀን መውጣቱ አይቀርምና በደመራው ተገለጠ። ኢትዮጵያም የገዛ ልጆቿ መውጋት ከጀመሯት ውለው አድርዋል። እናታቸውን መግረፍ ከጀመሩ ባጅተዋል። 'ያጠባ ጡቷን፣ ያጎረ እጇን' መንከስ ከጀመሩ ከራርመዋል። ሐቁን ሸሽገው ከል ካለበሷት ዓመታት ተቆጥረዋል። ግን የኢትዮጵያ ዕውነቶች እንደተዳፈኑ አይቀሩም፤ ይገለጣሉ። እንደ ንግስት ኢሌኒ በፍቅር የተቃጠሉ ልጆቿ ደመራዋን ለኩሰው ሐቋን ተምሶ ከተቀበረበት ቁልቁለት ማውጣታቸው አይቀሬ ነው።
የአዲስ ተስፋ፣የፍቅርና የአብሮነት መገለጫ በዓል- "ጊፋታ"
Sep 23, 2022 269
በፍሬዘር ጌታቸው (ከወላይታ ሶዶ) የበርካታ የማይዳሰሱ ቅርሶች ባለቤት ነው የወላይታ ብሔር። የብሔሩ የዘመን መለወጫ በዓል ''ጊፋታ'' በየዓመቱ በድምቀት ከሚከበሩ በዓላት መካከል አንዱ ነው፡፡ ጊፋታ የአዲስ ተስፋ ፍንጣቂ ተምሳሌት፣ የፍቅርና የአብሮነት መገለጫ እንዲሁም ወደ አዲስ ዓመት በአዲስ መንፈስ መሸጋገርን የሚያበስር ታላቅ በዓል ነው። የታሪክ ድርሳናት እንደሚያስረዱት ጊፋታ የወላይታ ሕዝብ በኦሞ ወንዝ ተፋሰስ ቋሚ ኑሮ ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ሲከበር የቆዬ ከማንኛውም እምነትም ሆነ የአምልኮ ሥርዓት ጋር ግኑኝነት የሌለው የዘመን መለወጫ ክብረ በዓል ነው፡፡ ለበዓሉ ታሪካዊ አመጣጥ ሁለት ዋና ዋና መላምቶች ይነገራሉ። የመጀመሪያው በወላይታ መንግሥት ተመስርቶ ግዛቱን ተቆጣጥሮ መኖር ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ በንጉስ “ካዎ ቢቶ” ዘመነ መንግስት ሲከበር እንደነበር የሚያስረዳ ሲሆን ሁለተኛው መላምት ደግሞ “በሞቼና ቦራጎ” ዋሻ እየተደረገ ካለው የአርኪዮሎጂ ጥናት ውጤት ጋር የሚያያዝ መሆኑ ይነገራል። ጊፋታ በወላይታ ብሔር ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ የመጣ የብሔሩ የማንነት መገለጫ ነው። የአሮጌው ዓመት ማብቅያና የአዲሱ ዓመት መጀመሪያ የመሸጋገሪያ በዓል ነው ጊፋታ። ጊፋታ ታላቅ፣ መጀመሪያ፣ መሻገር እንደ ማለት ነው። በወላይታ ብሔር የዘመን አቆጣጠር ጊፋታ የዓመቱ የመጀመሪያ ወር ስያሜ ነው፡፡ የወላይታ ብሔር የጊፋታን በዓል ማክበር ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ዓመቱን ሙሉ በስራ ካሳለፈ በኋላ በተለይም በዓመቱ መገባደጃ ያለውን ከባዱን የክረምት ጎርፍ፣ጉምና ጭጋግ በማለፍ ከክረምት፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን ወደ አዲሱ ዓመት በሰላም ላሸጋገረው አምላኩ ምስጋና የሚያቀርብበት ነው። እያንዳንዱ የማህበረሰብ አባል በጊፋታ በዓል ዝግጅት የየራሱ የሥራ ድርሻ አለው። ሁሉም የቤተሰብ አባላት ሥራዎችን በዕድሜና በጾታ ተከፋፍሎ ይከውናል። የበዓሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራም በማህበር ወይም በደቦ ሆኖ አንዱ ሌላውን በማገዝም ይሰራል። በዓሉ ከሌሎች በዓላት በተለየ መልኩ የረጅም ጊዜ ቅድመ ዝግጅት ይደረግለታል፡፡ የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የታሪክና ቅርስ ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ዶክተር አበሻ ሽርኮ የወላይታ ብሔር የዘመን መለወጫ በዓል የሆነው ጊፋታ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ፋይዳው የጎላ ነው ይላሉ። በጊፋታ ዕለት ወንዶች በሬ ከታረደ በኋላ በታረደው በሬ ቆዳ ላይ ተቀማጭ ገንዘብ ማሰባሰብ ይጀምራሉ፡፡ ዓመቱ ሲጠናቀቅ በተሰበሰበው ገንዘብ በሬ ከገዙ በኋላ የሚተርፈውን ገንዘብ ለቤት ውስጥ ወጪ ይጠቀማሉ፤ ለምግብነት የሚውሉ የምግብ ዓይነቶችን በዘር ወቅት መዝራት መሰብሰብና ለጊፋታ ወቅት ለይቶ ማስቀመጥ፤ ለማገዶ የሚሆኑ እንጨቶችን መሰብሰብ፣ በጊፋታ ወቅት ለከብቶች የሚሆን የሳር መኖ ማዘጋጀት፣ በዓሉ ሲቃረብ ለልጆች አዳዲስ ልብሶችን መግዛት፤ ለቅመማ ቅመም መግዣ የሚሆን ገንዘብ ለእናቶች መስጠት የአባዎራዎች ተግባር ነው። የአካባቢ እድሳት ሥራም በአባወራዎችና በወንድ ልጆቻቸው የሚከናወን ተግባር ነው። አዲስ ዓመት የመታደስ ምልክት ነውና የመኖሪያ ቤቶች የሳር በአዲስ ይቀየራሉ፣ አዳዲስ የቤት ውስጥ መገልገያ እቃዎች ይገዛሉ በመኖሪያ ቤት ዙሪያና በአካባቢው የጽዳት ሥራዎች ይከናወናሉ። የደለቡ በሬዎችን እና ሌሎች ለበዓሉ ድምቀት የሚያስፈልጉ ግብዓቶች የሚሸጡበት፣የዕደ-ጥበብ ባለሙያዎች ስራቸውን ለገበያ የሚያቀርቡበት በዓል ነው ጊፋታ። በበዓሉ የእርድ እለት ለበዓሉ ቀደም ተብሎ በአባወራዎች የሚጀመር የቁጠባ ባህል የዜጎችን የኢኮኖሚ አቅም የሚያጠናክር መሆኑን የገለጹት ዶክተር አበሻ፤ የቁጠባ ሥርዓቱ የ ጊፋታ በዓል ከተጠናቀቀ በኋላ በየሳምንቱ እስከ ምቀጥለው ዓመት የጊፋታ ገበያ ድረስ የሚቀጥል መሆኑን ያሰረዳሉ። እናቶችም ከምግብ ቅቤ ጀምሮ በርካታ ግብዓቶችን ከጎረቤቶቻቸው ጋር በእቁብ በመቆጠብ በዓሉ ሲደርስ ለገበያ ያቀርባሉ።በሽያጭ የሚያገኙት ገቢም ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን ከፍ እያደረገ መሆኑን ያስረዳሉ። እንደ ወንዶቹ ሁሉ እናቶች ከበዓሉ በኋላ ለቀጣይ ዓመት በየሳምንቱ ቁጠባው በመቀጠል ከሰኔ ወር ጀምሮ ለቆጮ፣ ለሙቹዋ፣ ለባጪራና መሠል ባህላዊ ምግቦች የሚውል እንሰትን በህብረት በመፋቅ እንደሚያዘጋጁ አመልክተው ይሄም የህብረት ስራን ከማጎልበት አንጻር ያለው ፋይዳ የላቀ መሆኑን አስረድተዋል። ያለፈውን ዓመት የመንግስትና ስራ አፈፃፀም በህዝብ ዘንድ መገምገም ሌላው በጊፋታ በዓል የሚከናወን ተግባር ነው። ይሄም በሥራ እንቅስቃሴዎች ህዝቡ ያስተዋላቸውን ክፍተቶች የሚተችበትና የማስተካከያ ሀሳቦችን የሚሰጥበት፣ የተሻለ አፈጻጸም ያለው የሚበረታታበት ለአዲሱ ዓመት በአዲስ የስራ መንፈስ መነሳሳት የሚፈጠርበት ነው ብለዋል። ጊፋታ አዲሱን ዓመት በአዲስ ተስፋ በአዲስ መንፈስ መቀበልን የሚያበስር መሆኑን አመልክተው፤ በበዓሉ ላይ በህብረት የሚከናወኑ ተግባራት አብሮነትን በይበልጥ የሚያጠናክሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። አዲሱ ዓመት ሁል ጊዜ አዲስ ተስፋ ይዞ እንደሚመጣ ስለሚታመን በንጹህ መንፈስና በንጹህ አካል ለመቀበል በ ጊፋታ ዋዜማ እኩለ ሌሊት ላይ ሁሉም የማህበረሰቡ አባላት ከአሮጌው ዓመት እድፍና ቆሻሻ ጋር አዲሱን ዓመት አንቀበልም በሚል እምነት ውኃ አሙቀው ገላቸውን እንደሚታጠቡ ያስረዱት ደግሞ የወላይታ ዞን የባህልና ቱሪዝም መምሪያ የባህል ታሪክና ቅርስ ስራ ሂደት ቡድን መሪ ከቶ አዳነ አይዛ ተናግረዋል። ይሄን የሚያደርጉትም አዲሱ ዓመት በሽታ፣ረሃብ፣ድርቅ የሌለበት መልካም ዝናብ የሚዘንብበት፣መልካም ነፋስ የሚነፍስበት፣የጥጋብ ዓመት እንዲሆን ካለፈው ዓመት ኃጥያት መንጻት አለብን ተብሎ ስለሚታመን መሆኑን አስረድተዋል። ሐሬ ሀይቆ፣ ቦቦዶ፣ ጎሻ እና 'ቃኤ ጊያ የ ጊፋታ በዓል መቃረቡን የሚያበስሩ በእንቅስቃሴያቸው ከወትሮ የተለዩ የገበያ ቀናት መሆናቸውን አብራርተዋል።ወቅቱ በህብረተሰቡ የጊፋታ በዓል ዝግጅት ሸመታና ሽያጭ የሚጀመርበት መሆኑን አምልክተው፤ የገበያ ቀናቱ አልባሳት፣ ቅቤ፣ ሠንጋ በሬ፣ ጌጣ ጌጦች፣ የስፌት፣ የሸክላ፣ የብረታ ብረት ምርቶችና የተለያዩ ለምግብነት የሚውሉ ግብአቶች የሚገዛባቸውና የሚሸጥባቸው እጅጉን የደሩ የገበያ ቀናት መሆናቸውን አስረድተዋል። ማህበረሰቡ የተለያዩ የባህላዊ ምግቦችን፣ ዳታ በርበሬ፣ ቦርዴ፣ጠላ፣ ጠጅ፣ቃሬቦ እና ወተት መጠጦችን በትልቅ እንስራ በማዘጋጀት የፍቅር ማዕድ በጋራ ይመገባሉ። ወጣት ወንዶች "ጉሊያ" ለሚሰኘው የደመራ ዝግጅት እንጨት ከመቁረጥና ከማቆም ጀምሮ የከብቶችን ሣር በማጨድና በመከመር፣ እንጨት በመፍለጥ ለበዓሉ ጊዜ ከማስቀመጥ አልፎ ከዘር እና ከአጨዳ ወቅት ጀምሮ ሁሉንም የጊፋታ ዝግጅት ስራዎችን በጊዜ በመከፋፈል ያከናውናሉ። የወላይታ ዞን የሀገር ሽማግሌ አቶ አብርሃም ባቾሬ በበኩላቸው ጊፋታ የእርቅ፣ የሰላምና የአንድነት መገለጫ በዓል መሆኑን ይናገራሉ። ጊፋታ የተጣሉ ባለትዳሮች፣ ቤተሰቦች፣ ጎረቤቶች እንዲሁም የአካባቢው ሰው የሚታረቅበት ወቅት ሲሆን አዲስ ጎጆ ለመቀለስ የተጫጩም ለቤተሰብ የሚያሳውቁበትና ሶስት ጉልቻ የሚመሰርቱበትም ጭምር ነው። በጊፋታ ጥላቻና ቂም ስፍራ የላቸውም ያሉት የሀገር ሽማግሌው ረጅም ጊዜ ሳይከፈል የቀረ ዕዳም ቢኖር በጊፋታ ለባለቤቱ ይመለሳል ብለዋል። በበዓሉ በተለያየ ምክንያት ከአካባቢው ርቀው የቆዩ ሰዎች ወደ ቀያቸው የሚመለሱበትና አዲሱን ዓመት በፍቅር በደስታ በአንድነት የሚቀበሉበት በዓል መሆኑን አስረድተዋል። የጊፋታ በዓል ከመስከረም 14 እስከ 20 ድረስ ባሉ ቀናት በሚውለው እሑድ ቀን የሚከበር መሆኑን አመልክተው ከበዓሉ በፊት ያሉት የሐሙስ የአርብና ቅዳሜ ቀናት የራሳቸው ባህላዊ እሴት ያላቸው የስራ ቀናት መሆናቸውን አስረድተዋል። እነዚህም “ኮሴታ ሃሙሳ” ፣ "ሱልኣ አርባ"ና "ባጪራ ቄራ" የሚል ስያሜ ያላቸው ናቸው ብለዋል።በነዚህ ቀናት ለቦርዴ የሚሆን እህል፣ ለሆድ ማሟሻ ጎዳሬ (Boynaa Cadhdhiyaa)ና ከቦዬ የሚዘጋጅ (Boyyiaa Pichaata)፣ ባጪራ፣ ሙቹዋ፣ ጉርዱዋ የሚዘጋጅባቸው መሆናቸውን አብራርተዋል። የጊፋታ በዓል ጎረቤትና ዘመድ አዝማድ የሚሰባሰብበት፣ ፍቅራቸውን ከአንድ ማዕድ በመቁረስ የሚያድሱበት ለበዓሉ ከተዘጋጀው መጠጥ የፍቅር መግለጫ በሆነው የ”ዳጌታ” ሥርዓት የሚጠጣበት ሰላምና ፍቅር የሚሰፍንበትና አዲስ ተስፋ የሚፈነጥቅበት የአዲስ ዓመት ማብሰሪያ ነው። እንደ አቶ አብርሃም ገለፃ ከጊፋታ ቀጥሎ የሚመጣው ሁለተኛው ቀን ማክሰኞ “ጪሻ ማስቃይኖ” የሚሰኝ ሲሆን ሰዎች የመልካም ምኞት አበባ ስጦታዎችን የሚለዋወጡበት ቀን ነው፡፡ በጊፋታ ወቅት የሚፈኩ አበቦችን ሲቀበሉ ካመት ዓመት ድረስ "ጊፋታ"ን እናንተ ቆጥራችሁ አክብሩት እንጂ ጊፋታ አይቁጠራችሁ “Gifaatay Inttena Qoodoppo Initte Gifaataa Qoodite” በማለት ይመራረቃሉ። እንዲህ እንዲህ እያለ የጊፋታ በዓል መገባደጃው ይደርስና ከበዓሉ ጋር ተያይዞ በነበረው የመዝናኛ ወቅት ሰዎች ከስራ እንዳይዘናጉ ሁሉም ችቦ እያቀጣጠለ ለሚመጣው በዓል አምላክ በሰላም እንዲያደርሰው በመመኘት ጊፋታን ይሸኛል፡፡ የጊፋታ በዓል ለአብሮነትና ለሰላም እንዲሁም የስራ ባህልን ጠንካራ ለማድረግና ግብረ ገብነት ለማጎናጸፍ ያለው ፋይዳው የጎላ መሆኑን የተናገሩት አቶ አብርሃም በተለይም ዜጎች ነገን በተስፋ በማየት ለስኬት እንዲበቁ ከማድረግ አንጻር ያለው ተፈጥሮአዊ አቅም ወሳኝ ነው ብለዋል።በመሆኑም እነዚህ ቱባ ባህሎቻችንን በአግባቡ በመጠቀምና ለትውልድ በማሻገር የሀገርን ከፍታ ማረጋገጥ እንደሚገባ አመላክተዋል።
ከውልደት እስከ ሞት በሽብር እና በውሸት
Sep 18, 2022 198
የህወሃት የሽብር ቡድን ‘የማጠቃለያ ምዕራፍ አካሄድና ስትራቴጂ’ በሚል ርዕስ ያዘጋጀው ሰነድ ነሃሴ 8 ቀን 2014 ዓም ሾልኮ መውጣቱ ይታወሳል፡፡ ቡድኑ ባዘጋጀው በዚህ ሰነድ ላይ ከውልደት እስከ ሞት በሽብር እና በውሸት እንደሚዘልቅ በይፋ ያስመሰከረበት ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ቡድኑ ቅጥፈት በተሞላበት ሰነዱ ላይ የእምዬን ወደ አብዬ አይነት የሚመስሉ ሀሳቦችን አስፍሯል፡፡ በዚህም ትክክለኛ የፋሺስት ተግባር እየፈጸመ ያለው ራሱ ሆኖ ሳለ የፌዴራል መንግስቱን ፋሺስት ሲል ይጠራል፡፡ ለዚህም ወረራ በፈጸመባቸው የአማራ እና አፋር ክልሎች በሰው፣ በእንስሳት እና በንብረት ላይ በቀጥታ የፈጸመውን እንዲሁም በደቡብ፣ በኦሮሚያ እና በሌሎች አካባቢዎች በቀጥታ እና በተልዕኮ የፈጸማቸውን እና ያስፈጸማቸውን ዘግናኝ ጥቃቶች፣ ዘረፋዎች እና ውድመቶች ማንሳት ለፋሽታዊ ተግባሩ ከበቂ በላይ ማሳያ ነው፡፡ ቡድኑ ለህዝብ ጥቅም እንዳልቆመ ግልጽ ሆኖ የታየው ህዝብ ሲያነሳ የነበረውን የለውጥ ጥያቄ ወደ ጎን በመተው ህዝብን በማፈን በለመደው ለዘረፋ የሚመቸው የስልጣን ማማ ላይ ለመቆየት ያልፈጸመው እና ያላስፈጸመው ወንጀል ምን አለ? ያልሰነዘረው የቱን የሽብር ጥቃትስ መጥቀስ ይቻላል? ቡድኑ በሁሉም ብሄር ብሄረሰቦች ትብብር በ2010 ዓ.ም በሀገሪቱ የመጣውን ለውጥ በመቃወም ወደ ጎሬው ከመግባቱ በፊትና ከገባ በኋላ ፌዴራሊስት ነኝ በማለት እንደለመደው በብሄር ብሄረሰቦች ስም ለመነገድ ያልቆፈረው ጉድጓድ ያላደራጀው ምስ ለኔም አልነበረም፡፡ ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ ሆነና ነገሩ በጊዜ ሂደት የሽብር ቡድኑን ውስጣዊ ሴረኝነት ሲረዱ ሁሉም አንተባበርህም በማለታቸው አንድም ልክ እንደሱ በሽብር ተግባራት ላይ ከተሰማሩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ አሸባሪ ቡድኖች ጋር ወዳጅነት መስርቶ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ህዝብን ማጥቃት ስራዬ ብሎ ተያያዘው፡፡ ይህ ቡድን ህብረ-ብሄራዊ/ፌዴራሊስት ነኝ ይበል እንጂ በተግባር የነበረው እና አሁንም ድረስ እየተከተለ ያለው የፖለቲካ መስመር ከአንድ እኔ በስተቀር ሌላ አያስፈልግም የሚል የስግብግብ እና የጥቅመኝነት አባዜውን ነው፡፡ ለዚህም አንድም አማራጭ ሃሳብ ያለው ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ በክልሉ እንዳይንቀሳቀስ ማፈኑን፣ ማሰሩን እና ማገዱን መጥቀስ ይበቃል፡፡ ይሁንና በርካታ ብሄር ብሄረሰቦችን አቅፎ የተመሰረተውን የፌዴራል መንግስት አሃዳዊ በሚል መጥራቱም እንዲሁ ቡድኑን ለትዝት ዳርጎታል፡፡ በአንድ ራስ ሁለት ምላስ የግሉ መገለጫ የሆነው ይህ የሽብር ቡድን ቀደም ሲል ከአማራ ህዝብ ጋር ቆጥረን ሂሳብ እናወራርዳለን ሲል በቆየበት አንደበቱ እንዲሁም በቅርቡ ሾልኮ በወጣው ሰንዱ የአማራ ተስፋፊ ሃይል በቆየ የትምክህት ታሪኩ፣ ተስፋፊነቱና ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን በሃይል ለመጫን የሚያደርገው እንቅስቃሴ እንደተጠበቀ ሆኖ ከወረራው በላይ፣ የተደራጀ ዘረፋ፣ ግድያና ሴቶችን የመድፈር የመሳሰሉ ወንጀሎችን ፈጽሟል ይላል። እነዚህን ህገ-ወጥ ተግባራት በተናጠልም ሆነ በጅምላ ሲፈጽም የቆየው ራሱ ሆኖ ሳለ ለሌላ መስጠቱ በርካቶችን አስገርሟል፡፡ አሁን የተፈጠረው አጋጣሚ በሌሎች ክልሎች ቢሆን ኖሮ ለትግላችን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ነበር። ነገር ግን ይሄ ሁኔታ የተፈጠረው በአማራ ክልል መሆኑ ከዚህ ሀይል ጋር ወዳጅነት ሊኖረን አይችልም፤ ይልቁንም በጠላትነት እንፈርጀዋለን ባለበት አፉ አሁን ላይ ደርሶ ከአማራ ህዝብ፣ ኤሊት፣ ፋኖ፣ ልዩ ሀይል ሆነ ሚሊሻ ምንም ጠብ የለንም ሲል የተለመደ መደለያ ለማቅረብ ሲሞክር ይደመጣል። የወጋ ቢረሳ የተወጋ አይረሳ የሚለውን ብሂል የዘነጋ በሚመስል መልኩ ይህን ማለቱ ትዝብት ላይ ጥሎታል፡፡ ቡድኑ ዕኩይ ዓላማውን ለማስፈጸም በዋናነት የሀሰት መረጃ ማሰራጨትን ጨምሮ ማድረግ የሚችለውን ሁሉ እንደሚያደርግ፤ መፈጸም የሚችለውን ሁሉ እንደሚፈጽም፤ መፍጠር የሚገባውን ጥምረት ሁሉ ከማንም ጋር ቢሆን እንደሚፈጥር በቃል ብቻ ሳይሆን በተግባር አሳይቷል። ለዚህም ነው በሰነዱ ላይ በተለይም የልዩነት ነጥቦችን በማህበራዊ ሚዲያ በማጉላት ህዝብ እና መንግስትን ለመነጠል ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራ አስረግጦ መጠቆሙ። ይህ የሽብር ቡድን ስልጣን ላይ በቆየበትም ሆነ አሁን በለየለት የሽብር ተግባር ላይ በተሰማራበት ወቅት በየደረሰበት መግደል፣ ሴቶችን መድፈር፣ ንብረት መዝረፍና ማውደም ግብሩ መሆኑን በቅርቡ ባወጣው ሰነድ ላይ በፈጸመው፣ ለሚፈጽመው የሽብር ተግባራት፣ ለንብረት ዘረፋ፣ ውድመት እንዲሁም ሀገር ለማፍረስ ሰርጎ ገቦችን በተፈናቃይና በተጓዥ ስም አስቀድሞ እንደሚልክ ነገር ግን ይህ ሰርጎ የሚገባው ሀይል ልክ እንደከዚህ በፊቱ የምዝበራና ዘረፋ ተግባር እንዳይሳተፍ ሲል የማስመሰል አቅጣጫ አስቀምጧል። ቀደም ሲል በአፍሪካ ህብረት የሚካሄደው የሰላም አማራጭ ህብረቱም ሆነ ልዩ ልዑኩ ከሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ልዩ ግንኙነት ያላቸው በመሆኑ ለእኔ አይጠቅመኝም። በአፍሪካ ህብረት ላይ እምነት የለኝም። የግድ የአሜሪካ፣ የአውሮፓ ህብረት እና የተባበሩት መንግስታት ተወካዮች ካላደራደሩ ሲል ቆይቶ በአፍሪካ ህብረት አመቻችነት በሚደረገው የሰላም አማራጭ ላይ ለመሳተፍ ተስማምቻለሁ ማለቱ እንደለመደው ዓለም አቀፉን ማህበረሰብ ለማደናገር ያስችለኛል ከሚል የተለመደ የክህደት ተፈጥሮአዊ ባህሪው የመነጨ መሆኑን ቡድኑ ያለፈባቸውን ጊዜያት በቅርበት ሲከታተሉ የነበሩ በርካቶች እየተናገሩት ይገኛሉ፡፡ ቡድኑ ክህደት እና ውሸት ጥርሱን ሲነቅል ያደገበት ሁነኛ መገለጫ ባህሪው መሆኑን ራሱ ባዘጋጀው ሰነድ ላይ በግልጽ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ችግሮችን በሰላም ለመፍታት ቁርጠኝነት እንዳለህ አስመስለህ እራስህን ማቅረብ መሆኑ ሊረሳ አይገባም በማለት በግልጽ አስቀምጦታል። ከዚህ መነሻነትም ቡድኑ መሰል ተግባራትን በስልጣን ላይ እያለም ጭምር ባዘጋጃቸው ተከፋይ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ሀሰተኛ የፈጠራ መረጃዎችን በማሰራጭት የዓለም አቀፉን ማህበረሰብ ሲያታልል መቆየቱን የሚናገሩም በርካቶች ናቸው፡፡ ቡድኑ ከጦርነት አባዜ ውጪ በሰላም ላይ የተመሰረተ ምንም አይነት ሰላማዊ ተሞክሮም፣ ልምድም ሆነ ፍላጎት እንዳልነበረው፣ እንደሌለውና ወደፊትም እንደማይኖረው የሚያመላክቱ በርካታ ማሳያዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ለዚህም በቅርቡ የፌዴራል መንግስት ህዘቡ ሰላም እንዲያገኝ በሚል የወሰዳቸውን ፖለቲካዊ የሰላም አማራጮች በሙሉ በመግፋት ህዝቡ ከጦርነት አዙሪት እንዳይወጣ ያደረገበትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ቡድኑ ለሰላም ያለውን አላርጂክነት ህዝቡም በጦርነት አዙሪት ውስጥ ተዘፍቆ እንዲቆይ ለማድረግ የቀረበውን የሰላም አማራጭ እንደማንቀበል ደጋግመን ለሕዝባችን ገልፀናል። የሕዝባችን ዘላቂ የሰላም ዋስትና የሚረጋገጠው በክንዳችን ብቻ መሆኑን በፅኑ እናምናለን በማለት የገለጸው፡፡ የሽብር ቡድኑ የያዘውን የግል እና የቡድን ፍላጎት ለማሳካት ምንም አይነት መጠን ያለው ህዝብ ቢያልቅ ደንታው እንዳልሆነ በሰነዱ ላይ የተጠየቀውን ያክል የሕይወት መስዋእትነት ህዝቡ እንዲከፍል እንደሚያደርግ አስፍሯል፡፡ ይህ የሽብር ቡድን ሀገር ለማፍረስ በሚከተለው አፍራሽ አካሄድና በንጹሃን ላይ በሚያደርሰው የሽብር ጥቃት ብቻውን እንዳልሆነና ሌሎች በህዝብ ደም ርካሽ ፖለቲካዊ ፍላጎታቸውን ለማሳካት ከተጠመዱ የውስጥና የውጭ ግብረ-አበሮቹ ጋር በቅንጅት እንደሚሰራም ለዚህ ደግሞ የራሳችንና የአጋሮቻችን ዝግጁነት ከመቼውም ጊዜ በላይ በተሻለ ሁኔታ ላይ ይገኛል። የውስጥ ትግላችን በማገዝ የሚንቀሳቀሱ እንደ ኦነግ የመሳሰሉ አጋሮቻችን እንዲሁም ዓለም አቀፍ አጋዦቻችን በዚህ ጊዜ የተሳካ ጥምረት በማድረግ በምናደርገው እንቅስቃሴ ከጎናችን መሆናቸውን የሚያረጋግጥ መሆኑን የክልላችን ዋና ስራ አስፈፃሚ በዝግ ባደረገው ውይይት አረጋግጧል ይላል። ይህ ቡድን ዕኩይ ዓላማውን ለማሳካት ወጣቶችን በተሳሳተ መረጃ ወደ ጦርነት መማገድን እንደስልት እንደሚጠቀም የትግራይ ወጣቶችን አሁን የሚደረገው ትግል ወደ አዲስ አበባ የሚደረግ የመጨረሻ ምዕራፍ ትግል እንደሆነ፤ ድል አይቀሬ መሆኑን መላው የትግራይ ክልል ወጣትና ሕዝቡን ማሳመን እንደሚገባ ገልጿል። በዚህም ቡድኑ ወላጆችን ያለ ጧሪ ቀባሪ ማስቀረቱን በተግባር አሳይቷል። አብዛኞቹ የሰብዓዊ ድጋፍ አቅራቢ ድርጅቶችም የሽብር ቡድኑ ተባባሪ መሆናቸውን ቡድኑ ባዘጋጀው ሰነድ ላይ በትግራይ የሚገኙ የዓለም አቀፍ የእርዳታ ድርጅቶች ለምናደርገው ትግል ደጋፊ እንዲሆኑና ከጎናችን እንዲቆሙ፤ ሰብአዊ ድጋፍ ማከማቻ መጋዘኖች በምናደርገው ትግል ወታደራዊ ስንቅ አቅርቦት እንዳይጓደል በቁጥጥራችን ስር ልናደርጋቸው ይገባል ሲል ጠቁሟል። በቅርቡ በሽብር ቡድኑ ነዳጅ ተዘረፈብኝ ያለው የዓለም ምግብ ድርጅት ተዘረፍኩ ከማለት ባለፈ በቡድኑ ላይ የወሰደው አንዳችም ርመጃ አለመኖሩን ላስተዋለ ትብብሩ መኖሩን ያረጋግጣል። ከዚህ በተጨማሪ ቡድኑ ከደረሰበት ወታደራዊ ኪሳራ እንዲያንሰራራ በሰብዓዊ ድጋፍ ስም የሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች እና ሌሎች አካላት እንደሚደግፉት ሲገልጽም፤ በውጭ ያሉ አጋዦቻችን በአስቸጋሪ እና አጣብቂኝ ጊዜ ውስጥም ቢሆን ችግሩን አልፈው ዘመናዊ ትጥቆች እንድንታጠቅ አድርገውናል ይላል። ይህ በስውርም ሆነ በግልጽ የተመሰረተ ግንኙነት ቀጣይነት እንደሚኖረው እና የጋራ ግባቸው በውጤታማነት እስኪጠናቀቅ ድረስም እንደሚቀጥል፤ የዚህ ዘመቻ ምዕራፍ መራርና በርካታ መስዋእትነት የሚጠይቅ በመሆኑ አሁንም ቀጣይነት ባለው ሁኔታ ዘመናዊ ትጥቅ ለመከላከያ ሃይላችን እንዲያቀርቡልን የሚያስችሉ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ከውስጥና ከውጪ ተባባሪዎቻችን ጋር ያለንን ስራ አጠናክረን መቀጠል ይኖርብናል ይላል። በመደበኛ ወታደራዊ አቅም ከፌዴራል መንግስቱ ጋር እንደማይመጣጠን ቀድሞ የተረዳው የህወሃት የሽብር ቡድን ሽብር፣ ፍርሃትና የስነ ልቦና ጫና መፍጠርን እንደስልት እንደሚጠቀም ለዚህም ተከፋይ የሆኑ የሀገር ውስጥ እና የውጪ መገናኛ ብዙሃንን እንደሚጠቀም ባለቤቶቻቸው አዲስ አበባ የሚገኙ ሚዲያዎችና ዩቲዩብ ቻናሎች ከፍተኛ ድጋፍ ስለሚኖራቸው የመረጃና ፋይናንስ ድጋፋችን ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ሲል በግልጽ አስቀምጧል። ለስልጣኑ መረጋገጥ ከሆነ ልማትን ማውደምም ሆነ ማደናቀፍ እንዲሁም ህዝብ መጎሳቆል ለቡድኑ ምኑም እንዳልሆነ መንግሥት በችግር ጊዜ አሳክቼዋለሁ የሚላቸውን የእርሻ ዘርፍም ሆነ የኢኮኖሚ ልእልና በማደናቀፍ ወደ ኋላ መመለስ፤ ሕዝብ በማንቀሳቀስ የጀመረው የእርሻ ልማት፣ ስንዴና ሌሎች የኢኮኖሚ ስራዎች ማደናቀፍ ላይ ትኩረት እናደርጋለን ይላል። ለዚህም የእርሻ ዘርፉ እንዲደናቀፍ በየአካባቢው ግጭት በመቀስቀስ እና ግጭት ለመቀስቀስ የሚያስችሉንን ሃይሎች በማገዝ እረፍት መንሳትን እንደስልት እንጠቀማለን ብሏል። ቡድኑ አሳካዋለሁ ላለው ዕኩይ ፖለቲካዊ ሴራዎች በማስፈጸሚያነት ከሚጠቀምባቸው ስልቶች መካከል ዋናው፤ በመንግሥት ላይ ሕዝብ እንዲያምፅና ፈጣን የስርአት ለውጥ እውን እንዲሆን ኢኮኖሚውን ማቃወስ ለነገ የማይባል ስራ ነው፤ የሚል ግልጽ የውንብድና ተግባርን ጠቅሷል። ለዚህም የተመረጡ አምራች ድርጅቶችንና መጋዝናቸውን ማጥቃትና ማፍረስ፣ ከእርሻ እስከ ገበያ ባለው ሂደት የዕለት አስቤዛ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ እንዲኖረው ማድረግ፣ ከውጪ የሚገቡ ሸቀጦች እና ነዳጅ እንዲስተጓጎል ማድረግ፣ ዋና ዋና የማስገቢያ ኮሪደሮች በመቆጣጠርና ሌሎች እርምጃዎችን በመውሰድ በሀገሪቱ የኢኮኖሚ ችግር እንዲፈጠር እና እንዲባባስ ማድረግ ዋናው ትኩረታችን እናደርገዋልን ይላል። መሰል የውንብድና ተግባር ከአንድ ከራሱ በላይ ለህዝብ ማሰብ ከማይችል አሸባሪ ቡድን የሚጠበቅ መሆኑን ሁሉም ከተረዳው ውሎ አድሯል። በመሆኑም መላ ህዝቡ መንግስት የሚሰራውን የመከላከል ስራ የማገዝ ተግባሩን አጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል። ከዚሁ ጎን ለጎንም የቡድኑን ዕኩይ ተግባር ማውገዝ፣ ማጋለጥና መመከት ይጠበቅበታል።