ቀጥታ፡
መጣጥፍ
በአረንጓዴ ልምላሜ ያጌጠው - የቤንቾች ቀዬ
Dec 3, 2025 490
በአረንጓዴ ልምላሜ ያጌጠው - የቤንቾች ቀዬ (በቀደሰ ተክሌ) -ከሚዛን ቅርንጫፍ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የሚገኘው የቤንች ምድር የሰጡትን የሚያበቅል ክረምት ከበጋ የማይጠወልግ ልምላሜን የታደለ ክልል ነው። በቤንች ሸኮ ዞን ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች ደን የሚመስልና በመኖሪያ መንደሮች የሚታየው አብዛኛው አረንጓዴ ስፍራ ለምግብነት የሚያገለግሉ ፍራፍሬዎች፣ ቅጠሎችና ስሮችን የያዘ ነው። የቤንቾች ቤት ዙሪያው በአረንጓዴ ተፈጥሮ ያጌጠ ነው። የቤታቸው ሞገስ፤ የምግብ ዋስትናቸውም ጭምር ነው። ከዚህ ከፍ ሲል ደግሞ ቤንቾች ነፋሻማ አየር እየማጉ የመኖር ልምድን ያጎናጸፋቸው ይኸው አፈር ቆፍረው ዘር ተክለው ያበቀሉትና የተንከባከቡት አረንጓዴ ሀብት ነው። ከአንድ አርሶ አደር ማሳ እንሰት፣ ሙዝ፣ ጎደሬ፣ ፓፓያ፣ አቮካዶ፣ ብርቱካን እና ሌሎች ፍራፍሬዎች ማየት የተለመደ ነው።   እግር ጥሎት ወደ ቀዬያቸው ያመራ እንግዳ ከፍራፍሬዎቹ የደረሰ ካለ ተቆርጦ ይሰጠዋል። በተጨማሪም ከብቶች፣ በጎችና ዶሮዎች የገቢ ምንጮቻቸው ናቸው። ወደ ቤታቸው ዘልቆ የገባ ሰው "ኪዥ" የተሰኘና የቤንች እናቶች ከወተት የሚያዘጋጁትን ''ጎደሬ'' ተብሎ ከሚጠራ የስራ ስር ምግብ ጋር ያጣጥማል። ቤንቾች በቆሎ፣ ማሽላ፣ ስንዴ፣ ባቄላ እንዲሁም ሌሎች የሰብል ዓይነቶችን ያለማሉ። ማር፣ ቡና፣ ኮረሪማ እና ሌሎች የተፈጥሮ ቅመማ ቅመሞችም ቤንቾች ከገበያ ገዝተው የሚያመጡት ሳይሆን ከማሳቸው የሚያፈሩት ነው። የተቀናጀ እርሻን ባህል ያደረጉት ብርቱ የቤንች አርሶ አደሮች ወደ ገበያ አውጥተው የሚሸጡት እንጂ የሚገዙት የለም ቢባል ማጋነን አይሆንም። የፋብሪካ ውጤቶችን ለመግዛትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግም ከጓዳቸው ሞልቶ የተረፈውን ወደ ገበያ አውጥተው በመሸጥ ገበያን ያረጋጋሉ። በጠንካራ የእርሻ ባህላቸውም ምክንያት ልጆቻቸው የበሰለ ምግብን ብቻ ሳይሆን የተለያዩ ፍራፍሬዎችንም ከጓሮና ከጫካ ቆርጠው ስለሚመገቡ ረሀብን አያውቁም።   የቤንቾች ቤት ዙሪያ ውብና ጽዱ ነው። ለዚህ ደግሞ ሴቶቹ የቤታቸውን ግድግዳ በተፈጥሮ ቀለም ከማስዋብ ጀምሮ ይጠበቡበታል። በቤንቾች ዘንድ የአንድ አርሶ አደር ጉብዝና የሚለካው በቤቱ ነው። ይህም የቤቱ ዙሪያ ያለው ውበትና የቤቱ ጥንካሬ ብቻም ሳይሆን ገላጣ መሆን አለመሆኑም ጭምር ከግምት ውስጥ ይገባል። አባዎራው በማሳው ላይ የሰብል ስራውን ያከናውናል። ልጆችና እማውራዋ ደግሞ ይኮተኩታሉ ያርማሉ። ከዚህም በተጨማሪ የቤንች እናት ጎደሬና ሌሎች የጓሮ አትክልቶችን የማልማት ኃላፊነት አለባት። የቤታቸው ዙሪያና ቀዬው በሙሉ በአረንጓዴ ልምላሜ አጊጦ የሚታይበት ምስጢሩ ይሄው ነው። ከርቀት ደን መስሎ የሚታየው አረንጓዴው ቀዬአቸው የገቢ ምንጭም በመሆኑ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ነውም ማለት ይቻላል። የሌማት ትሩፋት እሳቤ ቀድሞ የገባቸው ቤንቾች ማር አይገዙም፤ ለእንቁላል ሸመታም ገበያ አይወጡም። ወተት ቢያምራቸው በትኩሱ፤ ከዛም አለፍ ሲል በባህላዊ መንገድ እርሾ ጨምረው የሚያዘጋጁት "ኪዥ" የተሰኘ የወተት ውጤትን እንደ አይብም እንደ እርጎም አደርገው ይጠቀሙታል። የትኛውንም መልክዓ ምድር በሚስማማው የሰብል ዓይነት መሸፈን ያውቁበታል። መሬቱ ረግረጋማ ከሆነ ለጎደሬ፤ ዳገታማ ሆኖ ለማረስ የሚያስቸግር ከሆነ ደግሞ ለሙዝ ልማት ያውሉታል።   የምግብ ዋስትናን በቤተሰብ ደረጃ ለማረጋገጥ ሥራ የሚሠራው በጓሮ ነው። ይህም ሁሉን ከአንድ ጓሮ ለማግኘት በመጣር የሚመጣ ነው። ይህም ካልሆነ ደግሞ አስተማማኝና ቋሚ ምርት ማሳ ላይ አልያም ጎተራው ላይ ማኖር ያስፈልጋል። እንደ ቤንቾች በቤተሰብ ደረጃ ምግብን በራስ አቅም ለመቻል የሚደረገው ጥረት እንደሀገር ሲጠናከር ለውጡ ቀጣይነት ባለው መልኩ ይፋጠናን። ሀገራችን ኢትዮጵያ ካላት የሕዝብ ቁጥር አብዛኛው አርሶ አደር ነው። ይሁን እንጂ ጾሙን የሚያድር ሰፊ መሬት እንዳለ መረጃዎች ያመለከታሉ። አንድም መሬት ጾም እንዳያድር በየአካባቢው ስራዎች ቢጀመረም ውጤቱ ቀሪ ሥራዎችን የሚጠይቅ ነው። ዛሬም በምርት እጥረት የኑሮ ውድነትና መሰል ችግሮች ይስተዋላሉ። በእነዚህ መሬቶች ላይ ሰርቶ ከመለወጥ ይልቅ ከተማ ቁጭ ማለትን የሚሻ ትውልድ ማየት የተለመደ ነው። የቤንች ሸኮ ዞን አርሶ አደሮች እጃቸው ብርቱ በመሆኑ እነዚህ ችግሮች በስራ አሽንፈዋል። ይህም በምግብ ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ በኢኮኖሚም እንዲረጋጉ አድርጓቸዋል።   ለሀብት ምንጭ የሆነን ማሳ ለቆ ከተማ በመዋል የሚገኝ ነገር አይኖርም። በከተማም ሆነ በገጠር ለመለወጥ እንደ ቤንቾች ብርቱ እጆች ያስፈልጋሉ። ካልተሰራ ገቢ ሳይሆን ወጪ እያደገ ወዳልተገባ መንገድ ለመሄድ ምክንያት ይሆናል። ለችግርም ሆነ ሰርቶ የመለወጥ ዕድሉ የሚወሰነው በምርጫችንና ለሥራችን በምንሰጠው ትኩረት ነው። እንደ ቤንች ሸኮ ዞን አርሶ አደሮች ሰርቶ ለመለወጥና ራስን ለመቻል በየአካባቢው ያለን የተፈጥሮ ሀብት ወደ ልማት ለመቀየር ተግቶ መስራት ያስፈልጋል ። ሰላም!
ብልህ ከችግር ይማራል!!
Dec 2, 2025 326
ብልህ ከደረሰበት ችግር ይማራል!! በማሙሽ ጋረደው ገራድ ተስፋዬ ተፈራ ትውልድና እድገታቸው በሀድያ ዞን ሌሞ ወረዳ ቃልሻ ቀበሌ ሲሆን በ1999 ዓ.ም በህገ ወጥ መንገድ ከፍተኛ ገንዘብ አውጥተው ወደ ደቡብ አፍሪካ ተጉዘው እንደነበር ያስታውሳሉ። ገንዘብ ለማግኘትና የመለውጥ ህልማቸውን ለማሳካት በሚል ሩቅ አስበው የጀመሩት ህገ ወጥ ጉዞ መዳረሻውን እስር ቤት አደረገው። ይህም ሁኔታ ''ሩቅ አሳቢ-ቅርብ አዳሪ'' አደረጋቸው። በባዕድ አገር በነበራቸው የ2 ዓመት የእስር ቤት ቆይታም የምግብ እጦትን ጨምሮ አካላዊ ጥቃትና ጉልበት ብዝበዛ እንዲሁም የተለያዩ ስነ-ልቦናዊ ጉዳቶችን እንዳስተናገዱ ይናገራሉ።   ይህም አልበቃ ብሎ ከአካባቢው በህገወጥ መንገድ የሚሰደዱ ወጣቶችን ጉልበት በመጠቀም ሰፋፊ እርሻዎች ላይ እንዲሰማሩ በማድረግ የጉልበት ብዝበዛ ይፈፀምባቸው እንደነበርም ያስታውሳሉ። ብልህ ከደረሰበት ችግር ይማራል! የሚሉት ገራድ ተስፋዬ ሩቅ ሳይጓዙ፣ ገንዘብ ሳያወጡ ሰርተው መለወጥ የሚችሉበትን አካባቢያቸውን ፀጋ ሳያማትሩ ስደት መሄዳቸው ቁጭት ፈጥሮባቸው ነበር፡፡ ይህም በሀገራቸው እንኳንስ የለማን መሬት ይቅርና የተቦረቦረ መሬትን አልምቶ ጉልበትንና ጊዜን በአግባቡ ተጠቅሞ ለስኬት መብቃት እንደሚቻል ከእስር ቤት ቆይታቸው ተምረው ከእስር እንደተፈቱም ወዲያውኑ ወደ ሀገር ቤት መመለሳቸውን ተናግረዋል። በ2001 ዓ.ም ወደ ሀገር ቤት እንደተመለሱም በማህበር ተደራጅተው ከመንግሥት ባገኙት 70 ሺህ ብር ብድር በእንስሳት እርባታ ላይ ለመሰማራት 4 የወተት ከብቶችን ገዝተው የእርባታ ስራ መጀመራቸውን ይገልጻሉ፡፡   በዚህም የዞኑ አስተዳደር የሰጣቸውን መሬት አልምተው የእንስሳት እርባታውን አስፋፍተው መስራት ጀመሩ፡፡ አሁን ላይ የወተት ላሞቹን ቁጥር 37 በማድረስ የወተት ምርታማነታቸው አድጎ ከቤት ፍጆታ አልፎ ለሆሳዕና ከተማና አካባቢው በቀን ከ670 ሊትር በላይ ወተት እያቀረቡ ይገኛሉ፡፡ ለ40 ወጣቶችም ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል ከመፍጠራቸውም ባሻገር የተለያዩ የጭነትና የስራ ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ ከ250 ሚሊዮን ብር በላይ ሀብት ማፍራት መቻላቸውን ይናገራሉ። የጀመሩትን ስራ በጥምር ግብርና የማስፋትና የሚያገኙትን ወተት በማቀነባበር ምርቱን በተለያየ መልኩ ለገበያ የማቅረብ ራዕይን ሰንቀው በትጋት እየሰሩ ይገኛሉ፡፡ በህገወጥ ስደት ካጋጠማቸው ችግር ተነስተው በተግባር ያዩትን ለሌሎች በማስተማር የስደትን አስከፊነት ለአካባቢያቸው ወጣቶች እያስገነዘቡ መሆኑን ገልጸዋል።   ወጣቶች የስደትን አማራጭ ከመመልከታቸው በፊት የአካባቢያቸውን ፀጋ እንዲቃኙና ራዕይ ሰንቀው ራሳቸውን ለማሻሻል እንዲሰሩም መክረዋል። መለወጥ በውጪ ሀገር ብቻ ያለ የሚመስላቸው የቤተሰብ ኃላፊዎችም ልጆቻቸው በሀገራቸው ሰርተው መለወጥ እንደሚችሉ በማመን ሊያግዟቸው እንደሚገባም አቶ ገራድ አስገንዝበዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትልና የእርሻና ሆርቲካልቸር ዘርፍ ኃላፊ አቶ አለምይርጋ ወልደስላሴ፤ በክልሉ በርካታ ወጣቶች ያልተጨበጠ ተስፋ ሰንቀው ለህገወጥ ስደትና ለተለያዩ ችግሮች ተጋላጭ እየሆኑ ይገኛሉ ብለዋል፡፡   በሀገር ሰርቶ ለመለወጥ የሚያስችል አቅም በግብርናው ዘርፍ መኖሩን ጠቅሰው በዘርፉ የተሰማሩ ከስደት ተመላሾች በአካባቢያቸው ሰርተው ለስኬት እየበቁ እንደሚገኙም ጠቁመዋል፡፡ በዚህም ከራሳቸው አልፈው ለበርካታ ስራ አጥ ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር ላይ የሚገኙና የእነዚህን አካላት ተሞክሮ በመውሰድ በሀገር ሰርቶ ለመለወጥ መትጋት ይገባል ብለዋል፡፡
ዲጂታል ግብርና፤ የአፍሪካ ግብርና አዲስ ምዕራፍ
Dec 1, 2025 199
ዲጂታል ግብርና በጥቅሉ ሲተረጎም የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን ለግብርና ስራዎች መጠቀም ማለት ነው። ቴክኖሎጂዎቹ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ፣ የገበያ ተደራሽነትን በማስፋት፣ በአቅርቦት የእሴት ሰንሰለት ላይ መጠናከር፣ በቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት፣ የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምና የአየር ንብረት ለውጥ አይገበገሬነት ስራዎችን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አላቸው። የዓለም የዲጂታል ግብርና ገበያ እ.አ.አ በ2022 ከ10 እስከ 12 ቢሊዮን መድረሱን የተለያዩ መረጃዎች ያመለክታሉ። እ.አ.አ በ2028 የገበያ መጠኑ ከ23 እስከ 25 ቢሊየን ዶላር እንደሚደርስ ትንበያ ተቀምጧል። የዲጂታል ግብርና በአውሮፓ፣ በሰሜን አሜሪካ እና እስያ ፓሲፊክ በፍጥነት እያደገ ሲሆን በአፍሪካና ላቲን አሜሪካ ጅምር ላይ ነው ማለት ይቻላል። ሰሜን አሜሪካ 40 በመቶ እና አውሮፓ 25 በመቶ የዓለም የዲጂታል ግብርና ገበያ ድርሻን ይይዛሉ። አርሶ አደሮች ለዲጂታል ግብርና የሚያስፈልጋቸውን ቴክኖሎጂዎችን አለማግኘት፣ የዳታ ደህንነት እና የግል መረጃ ጥበቃ፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የኢንተርኔት ተደራሽነትና ባህላዊ ልማዶችን ከዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ጋር ማስተሳሰር ዓለም አቀፍ የዘርፉ ፈተናዎች ናቸው።   አፍሪካ ከአምስት እስከ ሰባት በመቶ(ከ500 እስከ 800 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር) የሚገመት ነው። በአፍሪካ የግብርና ቴክኖሎጂ ያለው ኢንቨስትመንት በፍጥነት እያደገ ይገኛል። ዘርፉ ከ400 ሚሊየን ዶላር መዋዕለ ንዋይ ፈሶበታል። በሞባይል የማማከር አገልግሎት፣ የገበያ ትስስር ማዕቀፎችና ለአርሶ አደሮች የፋይናንስ ቴክኖሎጂዎች ተደራሽ የማድረግ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። የቴክኖሎጂዎቹ የተደራሽነትና አላምዶ የመጠቀም ውስንነት፣ የመሰረተ ልማት ግንባታ፣ የፖሊሲ እና የህግ ማዕቀፍ እክሎች እንዲሁ አካታችነት የአፍሪካ ፈተናዎች ናቸው። በአፍሪካ አብዛኛው ግብርና በአነስተኛ ይዞታ ባላቸው አርሶ አደሮች ላይ የተመሰረተ ሲሆን ግብርና ለአፍሪካውያን ኑሮ እና የምግብ ዋስትና ወሳኝ የሚባል ነው። በዚህ ረገድም የዲጂታል ግብርና ለግብርና ምርታማነት ማደግ፣ የአቅርቦት እጥረትን በመቅረፍና የልማት ግቦች በማሳካት ረገድ የበኩሉን ሚና ይጫወታል። ኢትዮጵያ ለጉዳዩ ትኩረት በመስጠት በጥር ወር 2017 ዓ.ም የዲጂታል ግብርና ፍኖተ ካርታ ይፋ አድርጋለች። በወቅቱ የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ከግብርና ሚኒስቴር እና የጌትስ ፋውንዴሽን ጋር በመሆን ፍኖተ ካርታውን በጋራ ይፋ አድርገዋል። ማዕቀፉ ከዚህ ቀደም የነበሩ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴንሽንና ማማከር አገልግሎቶች በአንድ ጥላ ስር ያስቀመጠ ነው። ፍኖተ ካርታው የግብርና እሴት ሰንሰለቱን በሙሉ ዲጂታላይዝ የማድረግ አላማ አለው። የማማከርና የፋይናንስ አገልግሎቶች፣ የገበያ መረጃ፣ ዲጂታል ክህሎት፣ ሜካናይዜሽን፣ የዳታ መረጃ አሰባሰብና ዲጂታል መሰረተ ልማት የፍኖተ ካርታው አበይት ትኩረቶች ናቸው።   መንግስት ከልማት አጋሮች ጋር በመሆን የዲጂታል ግብርናን ለማስፋት እየሰራ ነው። የአፍሪካ ህብረት ያዘጋጀው የመጀመሪያው የዲጂታል ግብርና ጉባኤ በአዲስ አበባ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል። “ኢኖቬሽን እና የዲጂታል መፍትሄዎችን ለግብርና ዘርፍ በመጠቀም የአፍሪካን መጻኢ ጊዜ ብሩህ ማድረግ” የጉባኤው መሪ ሀሳብ ነው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊካ ሃዳዲ በጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር ኅብረቱ ዲጂታላይዜሽንን የልማት አጀንዳው አድርጎ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የግብርናው ዘርፍም በዚህ የዲጂታላይዜሽን አህጉራዊ ስትራቴጂ ውስጥ ትኩረት እንደተሰጠው አንስተዋል። ኮሚሽኑ አባል ሀገራት ለዲጂታል ግብርና የመረጃ አጠቃቀምና አስተዳደር አመቺ ፖሊሲዎችን እንዲያዘጋጁ እና እንዲተገብሩ ድጋፍ ያደርጋል ነው ያሉት። ለአርሶ አደሮች፣ ለግብርና ባለሙያዎችና ለወጣቶች በዲጂታል ክህሎቶች ዙሪያ ሥልጠና እንደሚሰጥም አረጋግጠዋል። በአፍሪካ ዲጂታል ግብርናን እውን ለማድረግ የአባል ሀገራት መንግስታት፣ የልማት አጋሮች፣ የግሉ ዘርፍ ተዋናዮች እና የምርምር ተቋማት በቅንጅት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።   የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ በበኩላቸው የአፍሪካን የግብርና ሥርዓት ለመለወጥ እና የምግብ ዋስትናን በዘላቂነት ለማረጋገጥ ዲጂታል ግብርናን መተግበር የግድ ነው ብለዋል። ዲጂታል ግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ የምርት ብክነትን ለመቀነስ፣ የፋይናንስና የገበያ ተደራሽነትን ለማስፋት እንዲሁም የመቋቋም አቅምን ለመገንባት ቁልፍ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ወጣቶች የአፍሪካ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ለኢኖቬሽንና ለዲጂታል ግብርና ትኩረት እንዲሰጡ ጠይቀዋል። ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ ትራንስፎርሜሽን ለማምጣት ዲጂታል ግብርናን እንደ ቁልፍ ስልት መውሰዷንና ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ዘርፉን ለማዘመን የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ በመድረኩ የተገኙት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ኢፋ ሙለታ(ዶ/ር) ገልጸዋል። የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎትን በስማርት ስልኮች አማካይነት ተደራሽ ማድረግ፣ ትክክለኛ የግብርና መረጃዎችን በአንድ ቋት መያዝና ማዘመን ላይ እየተሰራ መሆኑንና የግብርና ግብዓትን ተደራሽ ማድረግ፣ ከማሳ እስከ ገበያ ባለው ሂደት ውስጥ ያሉ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት ለማጎልበት ዲጂታላይዜሽን ላይ መሰራቱንም ጠቅሰዋል። የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ፣ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴሽን አገልግሎት፣ የግብርና ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን፣ የገበያ ተደራሽነት፣ የእሴት ሰንሰለትን ማጠናከር፣ የግብርና ምርታማነትን ከአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም መገንባት ጋር ያስተሳሰረ አካሄድን መከተል፣ የግብርና ፖሊሲዎችና የህግ ማዕቀፎች ትግበራ የኮንፍረንሱ ተሳታፊዎች የሚመክሩባቸው አጀንዳዎች ናቸው። ኮንፍረንሱ የእውቀት ሽግግር እና ፖሊሲ ተኮር ውይይቶች የሚደረግበት ሲሆን ስኬታማ የሀገራት የግብርና ኢኒሼቲቮች ለተሳታፊዎች ይቀርቡበታል። በአፍሪካ የዲጂታል ግብርና መፍትሄዎችን ተደራሽነት የሚደግፉ ስትራቴጂዎች የመለየት እና አጋርነቶችን ማጠናከር ከሁነቱ የሚጠበቅ አበይት ውጤት መሆኑን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የኢንተርኔት ተደራሽነት በሚፈለገው መጠን አለማደግ ፣ የዲጂታል ክህሎት ማነስ፣ የመሰረ ልማት ግንባታ እና የፖሊሲ ማዕቀፍ የዘርፉ ፈተናዎች ሲሆኑ ለአፍሪካ የዲጂታል ግብርና ትሩፋቶች ከፈተናዎቹ ይገዝፋሉ። ዲጂታል ግብርና ለአፍሪካ ዘላቂ ልማት፣ የምግብ ዋስትና መረጋገጥ እና ኢኮኖመሚ ልማት አንቀሳቃሽ ሞተር የመሆን አቅም አለው።
በቅሎ ወለደች
Nov 28, 2025 948
ቦንጋ፤ሕዳር 19/2017(ኢዜአ)፦ዛሬ ከወደ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ያልተለመደ ክስተት ታይቷል። ጉድ ሳይሰማ መስከረም አይጠባም እንዲሉ ጉዳዩ እንዲህ ነው፤ በክልሉ ዳውሮ ዞን ዛባ ጋዞ ወረዳ ያማላ ቦካ ቀበሌ አንዲት በቅሎ ወልዳለች። መውለድ ከማይችሉ እንስሳት ተርታ የምትመደበው በቅሎ የመውለዷ ነገር አዲስ ክስተት ሆኗል። ጉዳዩን በተመለከተ ኢዜአ ያነጋገራቸው የበቅሎዋ ባለቤት የሆኑት አቶ ነጋሽ በተላ በተፈጠረው ነገር እጅጉን መደናገጣቸውን ገልጸዋል። በቅሎ በተፈጥሮ እንደማትወልድ የሚታወቅ ቢሆንም በቤታቸው የተከሰተውን ነገር ማመን እንደከበዳቸው ነው የተናገሩት። ከወትሮ የተለየ ነገር እንዳላሳየችና ትላንትና ማታ ባልጠበቁት ሁኔታ ወልዳ መመልከታቸውን አቶ ነጋኝ አውስተው፤ በቅሎዋ ከወለደች በኋላ ምንም አዲስ ነገር እንዳላሳየችም አስረድተዋል። በዛባ ገዞ ወረዳ የማላ ቦካ ቀበሌ የእንስሳት ባለሙያው አቶ ደረጀ ደስታ ፤ ክስተቱ ከሳይንስና ከተፈጥሮም የሚቃረን ለማመን የሚከብድ መሆኑን ገልጸዋል። የተወለደው ፍጡር የፈረስ ቅርፅ ያለው ፣ ገና ፀጉር ያላበቀለና ቀኑ ያልደረሰ እንደሆነም አስረድተዋል። ሲወለድም የሞተ ሲሆን በቅሎዋ አሁን ላይ በሙሉ ጤንነት ላይ እንደሆነችና ምንም የተለየ ምልክት እንዳላሳየችም ነው ለኢዜአ የገለጹት። ይህን አዲስ ክስተት ከተመለከቱ የአካባቢው ነዋሪዎች መካከል የአቶ ነጋኝ ጎረቤት የሆኑት አቶ ባሳ ፈልታሞ፥ይህ ነገር ለማመን የሚከብድ ክስተት ነው፤ ከዚህ በፊት እንዲህ ዓይነት ነገር ሰምቼም ሆነ አይቼም አላውቅም ሲሉ ገልጸዋል።
ድንበር ተሻጋሪው የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር ወዳጅነት
Nov 27, 2025 253
ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1969 ነው። ሀገራቱ በተለያዩ ክፍለ አህጉራት የሚገኙ ቢሆንም ርቀት ሳይገድባቸው በዲፕሎሲ እና ኢኮኖሚ መስኮች ያላቸውን ትብብር ቀጥለዋል። ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር በተለያዩ መስኮች ያላቸውን ግንኙነት ለማስፋት እየሰሩም ይገኛሉ። ሲንጋፖር በፍጥነት እያደገ የመጣውን የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ፣ ስትራቴጂካዊ ስፍራና ከፍተኛ የህዝብ ብዛት በመጠቀም ትስስሯን የማጎልበት ጠንካራ ፍላጎት አሳይታለች። እ.አ.አ በ2017 የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን እና የሲንጋፖር የሕብረት ስራ ኢንተርፕራይዝ የተፈራረሙት የጋራ መግባቢያ ስምምነት የዚሁ ማሳያ ነው። ስምምነቱ ሲንጋፖር በኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማትና የንግድ ስራ ምቹነት ሪፎርሞች ልምዷን የምታካፍልበት ነው። ሎጅስቲክስ፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ግብርና ማቀነባበሪያ፣ ማዕድንና ቱሪዝም ትብብራቸውን ለማጠናከር የጋራ ስምምነት ላይ ከደረሱባቸው መስኮች መከላከል ይጠቀሳሉ። ኢትዮጵያ ለሲንጋፖር የአፍሪካ የኢንቨስትመንት መግቢያ በር፣ ሲንጋፖር ለኢትዮጵያ የእስያ መግቢያ በር ናቸው ማለት ይቻላል። ሁለቱ ሀገራት በተደጋጋሚ የንግድ እና ኢንቨስትመንትን ጨምሮ አጠቃላይ ትብብራቸውን ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል። ሌላኛው የሀገራቱ የትብብር መስክ አቪዬሽን ነው። የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር አየር መንገዶች እ.አ.አ በ2012 የአየር አገልግሎት ትብብር ስምምነት መፈራረማቸው ይታወቃል። ስምምነቱ የመንገደኞችና ካርጎ በረራዎችን እንዲሁም የትራንስፖርት ትስስርን ለማጠናከር የሚያስችል ነው። የአየር አገልግሎት ስምምነቱ በምስራቅ አፍሪካና በደቡብ ምስራቅ እስያ መካከል በጉዞ፣ በካርጎ ንግድ እና ሎጅስቲክስ ያለውን ትብብር ለማጎልበት ያስችላል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እ.አ.አ በ2024 በሲንጋፖር ይፋዊ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወሳል። ጉብኝቱ ሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩበት 55ኛ ዓመት ክብረ በዓል ጋር የተገጣጠመ ነበር። በጉብኝቱ ወቅት ኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር የጋራ መግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱ ሀገራቱ በመደበኛነት የሁለትዮሽ ምክክር እንዲያደርጉ፣ በትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ዘርፍ ያላቸውን ትብብር ማጠናከር የሚያስችል ነው። ሲንጋፖር በኢትዮጵያ ኤምባሲ እንደምትከፍት ይፋ አድርጋለች። የሲንጋፖር ውሳኔ ከኢትዮጵያ አልፎም ከቀጣናው ጋር በትብብር ለመስራት ያላትን የረጅም ጊዜ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ሆኗል።   የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ዎንግ በቅርቡ በአዲስ አበባ ይፋዊ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸው ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ከኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጋር በሁለትዮሽ እና በባለብዙ ወገን ትብብራቸው ዙሪያ መክረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ውይይቱ በሁለቱ ሀገሮች መካከል ያለውን ግንኙነት ለጋራ ነጋችን ወሳኝ በሆኑ መስኮች በጋራ ለመሥራት በምናደርገው ጥረት ውስጥ አንድ ጠቃሚ ርምጃ ነው ሲሉም ገልጸውታል። በተለይም በክሂሎት ልማት እና የካርበን ብድር ትብብር ላይ የተፈረሙት የመግባቢያ ስምምነቶች ጽኑ እና ለነገው ገበያ ዝግጁ የሆኑ ሠራተኞችን ለማፍራት ብሎም በአየር ንብረት ጥበቃ ረገድ ዘላቂ፣ ዝቅተኛ ካርበን የሚያወጣ እድገት ለማረጋገጥ ያለንን የጋራ አቋም ያንጸባርቃል ነው ያሉት። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም በላቀ ተግባራዊ ትብብር ንግድ እና ኢንቨስትመንትን በማስፋፋት፣ ዘመናዊ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስን በማልማት፣ በዲጂታል መሠረተ ልማት፣ በገንዘብ ልውውጥ ቴክኖሎጂ፣ ሳይበር ደኅንነትና ሰው ሰራሽ አስተውሎት ያለንን ትብብር ለመጠቀም እጅግ ሰፊ አቅም አለ ነው ያሉት። ሁለቱም መሪዎች በጉብኝቱ የኢኮኖሚ ትብብርን ለማላቅ፣ ተቋማዊ መስተጋብርን ለማጠናክር ብሎም የወል ቅድሚያዎቻቸውን ከፍ አድርጎ ለመከወን መንገዶችን እንደተመለከቱበትም ተናግረዋል። ሲንጋፖር በኢትዮጵያ ኤምባሲ ለመክፈት መወሰኗ ከኢትዮጵያ ባለፈ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ትስስር ማጎልበት የሚያስችላትን ማዕቀፍ እንደሚፈጥር የገለጹት ደግሞ የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ላውረንስ ዎንግ ናቸው። ከዚህ በፊት የሲንጋፖር ጠቅላይ ሚኒስትር ኢትዮጵያን የጎበኙት እ.አ.አ በ1964 እንደነበር አስታውሰው የሁለቱን ሀገራት ትብብር ማጠናከር እና ለሲንጋፖር አዳዲስ የንግድ በሮች መክፈት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውን አመልክተዋል። አስተዳደር፣ ትምህርት እና ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ሀገራቱ ግንኙነታቸውን ለማጠናከር ከሚፈልጉባቸው መስኮች መካከል እንደሚጠቀሱ አንስተው የሀገራቱ መሪዎቹ በተገኙበት ከቁልፍ የጋራ ፍላጎቶቻችን ጋር የሚጣጣሙ የክህሎቶች ልማትና የካርቦን ገበያ የጋራ መግባቢያ ስምምነቶችን ተፈራረመናል ብለዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሲንጋፖር በአዲስ አበባ ኤምባሲ ለመክፈት መወሰኗን በደስታ እንደተቀበሉት ተናግረዋል። የኤምባሲው መከፈት ሲንጋፖር ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ብቻ ሳይሆን ከአፍሪካ ህብረት እና ከመላው አፍሪካ ጋር ቁልፍ ትስስር መፍጠሪያ ሆኖ እንደሚያገለግልም አመልክተዋል። ሲንጋፖር እና ኢትዮጵያ የየቀጣናቸው መግቢያ በር ናቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገራቱ ያላቸውን አጋርነት የበለጠ በማጠናከር ዜጎችን በዘላቂነት ተጠቃሚ የሚያደርግ ድልድል በደቡብ ምስራቅ እስያ እና አፍሪካ መካከል እየገነቡ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ እና ሲንጋፖር የቅርብ ጊዜ ውይይቶችና የጉብኝት ልውውጦች ሀገራቱ በጋራ ለመልማትና ለማደግ ያላቸውን ቁርጠኝነት ያሳያል። የሁለቱ ሀገራት ትብብር በአፍሪካ እና በደቡብ ምስራቅ እስያ መካከል እንደ ድልድይ ሆኖ የሚያገለግል ነው።
በጥምር ግብርና ስኬት ያስመዘገቡት አርሶ አደር ወልዴ አርጋኒ
Nov 14, 2025 663
(በእንዳልካቸው ደሳለኝ - ከወልቂጤ ኢዜአ ቅርንጫፍ) በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጉራጌ ዞን ምሁር አክሊል ወረዳ ጨዛ ቀበሌ ነዋሪ ናቸው። ለዘመናት ባከናወኑት የግብርና ልማት ሥራ ኑሯቸው ከእጅ ወደ አፍ የዘለለ አልነበረም። ዛሬ ላይ ሆነው ያን ዘመንና ያሳለፉትን ዕድሜ ሲያስታውሱ ይቆጫሉ። በኋላ ቀር መንገድ ሲያከናውኑት ከነበረው የግብርና ልማት ሥራቸው ተጠቃሚ መሆንም፤ ሀብት ማፍራትም ሳይችሉ ቀርተዋል።   አርሶ አደር ወልዴ አርጋኒ ይባላሉ። ከሰበሰቡት ሰብል ጎተራቸው ሳይጎድል፣ ከእንስሳት እርባታ ስራቸውም ጥገታቸው ሳትነጥፍ ማየት የዘውትር ህልማቸው ነበር። ለም መሬት ይዘው ምርታማ ባለመሆናቸው ሲቸገሩ፣ የሚሰራ ጉልበት ይዘው ማዕዳቸው እየጎደለ የጎልማሳነት ዕድሜ መባቻ ድረስ ችግር ሲፈራረቅባቸው ዓመታትን አሳልፈዋል። ይህ ፍላጎታቸው ሰምሮ፣ ጓሯቸው ለምቶ፣ ቤታቸው ሞልቶና ጥሪት አፍርተው የማየት ውጥናቸው ሳይሳካ ዓመታት ቢቆጠሩም ዛሬ ግን በጀመሩት የጥምር ግብርና ሥራ ነገሮች ተቀይረዋል። የዓመታት ምኞታቸውን ማሳካት ጀምረዋል። ከስድስት ዓመታት በፊት በትንሽ መሬት ላይ የጀመሩት የጥምር ግብርና ሥራ ለስኬት እንዲበቁ ከማድረግ ባለፈ በአካባቢያቸው አርአያ የሆኑ አርሶ አደር አድርጓቸዋል። የጥምር ግብርና ስራቸው ለዓመታት ከነበሩበት ከእጅ ወደ አፍ ኑሮ በማውጣት ለአፍም ለኪስም ሆኗቸዋል። የመንግስት የልማት ትኩረት የሆነው ጥምር ግብርና በውስን መሬት ላይ የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በቅንጅት እንዲያለሙ እድል ፍጥሮላቸዋል። በዋናነት በሰብል፣ በእንሰት፣ በፍራፍሬና በእንስሳት እርባታ ላይ አተኩረው እየሰሩ ይገኛሉ። ይህም የአንዱ ክፍተት በሌላው እየተሞለ ውጤታማ ስላደረጋቸው የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ ነው። ለቤት ፍጆታ ብቻ ያመርቱ የነበረው የእንሰት ምርትን በማስፋፋት ችግኙንና ተረፈ ምርቱን በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ጭምር ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ሆነዋል። የግብርና ግብዓቶችንና ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ተጠቅመው በሚያመርቱት ገብስ ለሌሎች አርሶ አደሮች ምሳሌ መሆን ችለዋል።   ዝርያቸው የተሻሻሉ ላሞችን ስለሚያረቡም ወተት ከማጀታቸው አይጠፋም። በጓሯቸው የሚያለሙትን አትክልትና ፍራፍሬ ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ ማቅረብ የሚያስችል አቅም ፈጥረዋል። አርሶ አደሩ ከንብ ማነብ ሥራቸውም እንዲሁ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ነው። ከአካባቢው ስነምህዳር ምክንያት ብዙም ያልተለመደውን ቡና በመትከል ለፍሬ አብቅተዋል። የእሳቸውን ፈለግ የተከተሉ ሌሎች አርሶ አደሮችም ቡና ማልማት ጀምረዋል። በእጅ ያለን ሀብት ወደ ውጤት ለመቀየር ተግቶ መስራትና ጽናት ያስፈለጋል ያሉት አርሶ አደር ወልዴ፣ በግብርና ባለሙያዎች የተደረገላቸው ሙያዊ ድጋፍና የተፈጠረላቸው የገበያ ትስስር ለውጤታቸው ሚና እንዳለው ገልጸዋል። የእርሻ ልማትና የእንስሳት እርባታውን በቅንጅት ማከናወናቸውም እንዲሁ። አርሶ አደር ወልዴ የዓመታት ቁጭታቸው ዛሬ መፍትሄ እያገኘ ነው። የጥምር ግብርና ሥራቸው በምግብ ራሳቸውን እንዲችሉና ልጆቻቸውን በጥሩ ሁኔታ እንዲያሳድጉ አስችሏቸዋል። መኖሪያ ቤትን ጨምሮ የተለያየ ሀብት ለማፍራት ምክንያት በመሆኑም ልማቱን አስፋፍቶ ለማከናወን አቅደዋል።   አርሶ አደር ወልዴ አርጋኒ ለአካባቢው አርሶ አደሮች ጭምር አርአያ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የጉመር ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሙራዱ ብሩ ናቸው። ቀደም ሲል በገብስ ምርት ላይ ብቻ አተኩረው ይሰሩ የነበረውን የግብርና ሥራ እንዲቀይሩ ምክንያት እንደሆኗቸው ይገልጻሉ። ከአርሶ አደር ወልዴ በወሰዱት ልምድ ወደ ጥምር ግብርና ገብተዋል። በዚህም ድርቅ የመቋቋም አቅም ያለውን እንሰት በማሳቸው በስፋት ማልማት ጀምረዋል። የነበሯቸውን ሀገረሰብ የዳልጋ ከብቶች በተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎች በመቀየር የተሻለ ተጠቃሚ ለመሆን ተግተው እየሰሩ ነው። ጥምር ግብርና የተሻለ ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ከአርሶ አደር ወልዴ ተምሪያለሁ ይላሉ። ከኢኮኖሚ ጠቀሜታው ባለፈ የመሬት ለምነትን ለማስጠበቅም ጠቀሜታው የጎላ በመሆኑ የጀመርነውን ሥራ እናጠናክራለን ሲሉም ነው የገለጹት።   የሙህር አክሊል ወረዳ ግብርና ፅህፈት ቤት ሀላፊ መኑር ጀማል በበኩላቸው "አርሶ አደር ወልዴ አርጋኒ በውስን መሬት ገብስ፣ እንሰት፣ ቡና እና የተለያዩ ፍራፍሬዎችን በጥምር በማልማት የራሳቸውን ህይወት ከመቀየር ባለፈ ለሌሎች አርሶ አደሮች አርአያ እየሆኑን ነው ብለዋል። አርሶ አደሩ በሽታ መቋቋም የሚችሉና ለመድሃኒትነት የሚፈለጉ የእንሰት ዝርያዎችን በማፍላት ለገበያ እያቀረቡ ይገኛሉ። ከዚህም ባለፈ በመጥፋት ላይ የነበሩ የእንሰት ዝርያዎችን የመታደግና የአፈር ለምነት እንዲጠበቅ ጉልህ ሚና ማበርከታቸውንም ተናግረዋል፡፡ የጥምር ግብርና አሰራር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ስነ-ምህዳራዊ ጥቅሞችን የሚያስገኝ በመሆኑ በወረዳው ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ መሆኑን ነው የገለጹት። የአርሶ አደር ወልዴ ልምድን በማስፋት የሌሎች አርሶ አደሮችም ጓዳ ሞልቶ እንዲትረፈረፍ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው በተለይ በጥምር ግብርና አርሶ አደሩ ከራሱ ባለፈ ለሌሎች ጭምር እንዲተርፍ የማድርጉ ሥራ ይጠናከራል ብለዋል።   ልማቱ እርስ በእርስ የሚደጋገፉና በአንድ መሬት ላይ የተለያዩ ምርቶችን በማግኘት የተሻለ ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው። ግብርናን ለማዘመንና ምርታማነትን ለማሳደግ በሚሰራው ሥራ ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች ውስጥ በጥቂት መሬት ብዙ ማምረት መቻል ነው። በመሆኑም በተለይ የመሬት እጥረት ባለባቸው አካባቢዎች ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ጠቀሜታው የጎላ ነው። በሥራ ውጤታማ ለመሆን ሁሉም ነገር ምቹና አልጋ በአልጋ መሆን የግድ እንዳልሆነ አርሶ አደሩ ጥሩ ማሳያ ናቸው። ወጣቶች በአካባቢያቸው ያለውን ዕድል እንዴት ወደሀብትነት መቀየር እችላለሁ ብለው ከሰሩ ውጤታማ እንደሚሆኑ የእሳቸው የስኬት ጉዞ በቂ ማሳያ ነው። ሰርቶ ለመለወጥም ሆነ ሀብት ለማፍራት ችግሮችን በጽናት ማለፍ እና የሥራ ትጋት ወሳኝ ነውና ተሞክሯቸውን ማስፋት ያስፈልጋል።
  "ከትውስታ ወደ አዲስ ተስፋ"
Nov 12, 2025 593
"ከትውስታ ወደ አዲስ ተስፋ" ብርሃኑ ፍቃዱ -ከሰቆጣ የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ መልካዓምድራዊና ኢኮኖሚያዊ መሰረት ያለው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒሰትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በቅርቡ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ ላይ ማብራራታቸው ይታወሳል። ኢትዮጵያ የባህር በሯን ያጣችበትን የ30 ዓመታት ታሪክ ለመቀልበስ ይህን ያህል ዓመት እንደማይወስድ አጽንኦት ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ የባሕር በር ያጣችበት መንገድ ሕጋዊና ተቋማዊ መሰረት የሌለው የሚያስቆጭ ብሔራዊ ጥቅም ስብራት አካል ስለመሆኑም አንስተዋል። አቶ መለሰ ይሄይስ እና አቶ አድማሱ ደሳለኝ፤ የኢትዮጵያ የባሕር በር የተወለዱበት ስፍራ፣ የኖሩበት ቀዬ፣ ያሳደጋቸው ማህበረሰብ ... የዘመናት ትዝታና ትውስታቸው እንደሆነ ይገልጻሉ። ይህን የታሪካቸው አካል የሆነውን የባሕር በር ማጣትም የሁል ጊዜ ፀፀትና እንደ ሰውነት ጥላ አብሮዋቸው የሚዞር እውነታ ነው። ከአካባቢው ርቆ ለሚገኝ ሰው ትውስታውን ሲያወራ ለሌላው ተረት ተረት፤ ለራስ ደግሞ የውስጥ ቁስል ማገርሸት ሆኖ ነው የሚሰማው ይላሉ።   ኢትዮጵያም የአሰብ ወደብንና የቀይ ባህር መዳረሻን በፖለቲካዊ ሸፍጥ ማጣቷ በቀይ ባህር ላይ እየዋኙ፣ ውሃ እየተራጩ፣ በዳርቻው ነፋሻማ ስፍራ እየተዝናኑ... ለኖሩት ለእነ መለሰ እና አድማሱ መቼም የማይረሳ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የባሕር በር ጉዳይ ለኢትዮጵያ የህልውና ጉዳይ መሆኑን ለአለም ማሕበረሰብ ጥያቄውን ሲያሳውቁ ተደብቆ ለቆየው ትውስታቸው አዲስ ተስፋ እንደሰጣቸውም ለኢዜአ ተናግረዋል። አቶ መለሰ ይሄይስ በአሰብ የነዳጅ ማጣሪያ ማዕከል ለ12 ዓመታት እንዳገለገሉ በትውስታና ቁጭታቸውን ወደ ኋላ ተመልሰው ያወሳሉ። አሁን በሰቆጣ ከተማ የሚኖሩት አቶ መለሰ ይሄይስ ፤ የአሰብ ወደብ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ በማፋጠን የበኩሉን አስተዋጽኦ በማበርከት ተደማሪ አቅም ነበር በወቅቱ ይላሉ።   ይህን የአሰብ ወደብንና የቀይ ባሕር መዳረሻን በፖለቲካዊ ሴራ ኢትዮጵያ ስታጣ ይሰሩበት ከነበረው የአሰብ የነዳጅ ማጣሪያ ስራ አቁመው ወደ ትውልድ ስፍራቸው ሰቆጣ መምጣታቸውን አውስተዋል። በራሳቸው ላይ ከደረሰባቸው የስራ እና ሃብትና ንብረት ማጣት ፣ እንግልትና ሌሎች ችግሮች በላይ ኢትዮጵያ ከባሕር በር የተነጠለችበትን ሁኔታ ሲያስቡና ሲያሰላስሉ እንደሚያስቆጫቸው ይገልጻሉ። ኢትዮጵያ የቀይ ባሕርን በማጣት የባሕር በር ብቻ ሳይሆን የገቢና ወጭ ንግድን፣ የነዳጅ ማጣሪያ ጭምር ነው ያጣችው ያሉት አቶ መለሰ፤ አሁን ጥያቄው መነሳቱ ኢትዮጵያን ወደ ቀደመ ገናናነቷ ለመመለስ ያለመ አበረታች ተግባር እንደሆነ ተናግረዋል። መንግስት ያነሳው የባሕር በር ጥያቄም የዘመናት ቁጭታችንን፣ ብስጭታችንን እና ህልማችንን ከተደበቀ ትውስታ፤ ወደ አዲስ ተስፋ የወሰደ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ ህጋዊና ታሪካዊ ነው ያሉት አቶ መለሰ ፤ ጥያቄው በሰላማዊ መንገድ እልባት እንዲያገኝም ለአዲሱ ትውልድ በማስተማርና ግንዛቤ በመፍጠር የበኩላቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል።   ከ1973 ዓ.ም ጀምረው ለአስር ተከታታይ ዓመታት በአሰብ ወደብ የሲቪል መሃንዲስ ክፍል ሰራተኛ እንደነበሩ ያወሱት አቶ አድማሱ ደሳለኝ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የባሕር ባር ባለቤት በሆነችባቸው ዘመናት ገናና እና የተከበረች ሀገር ሆና መቆየቷን አንስተዋል። የባሕር በሩ የኢትዮጵያ የገቢና ወጭ ንግድ የሚሳለጥበት እንደነበር አስታውሰው፤ ይሄን ታላቅ ትሩፋትና ፀጋ ለማስመለስ የተጀመረው እንቅስቃሴ ቁጭትና ትውስታችንን ወደ አዲስ ተስፋ የቀየረ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በታሪካዊ ጠላቶችና ባንዳዎች እኩይ ሴራ የባሕር በር ካጣች ወዲህ ጥያቄውን ማንሳት የማይቻልበት የአፈናው ዘመን አክትሞ በለውጡ መንግስት መነሳቱ አበረታችና ለማስመለስም ከፍተኛ መነቃቃት የፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። እኔም ባለኝ አቅም ሁሉ ስለባሕር ባር አስፈላጊነት፣ ጥቅምና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ግንዛቤ በመፍጠር ለስኬታማነቱ የድርሻዬ እወጣለሁ ሲሉም ገልጸዋል።
​​​​​​​ባሕር በር -የታሪክና የእድገት ስብራት ወጌሻ 
Nov 5, 2025 654
ባሕር በር የታሪክ እና የእድገት ስብራት ወጌሻ በቀደሰ ተክሌ የምሥራቅ አፍሪካዋ ታላቅ ሀገር ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ስሟ ገኖ እንዲነሳ ካደረጓት መካከል የሰው ዘር መገኛነት፣ የራሷ የሆነ የአስተዳደር ሥርዓት፣ የዘመን አቆጣጠር፣ ቋንቋና ፊደል ያላት ሉዓላዊት ሀገር መሆኗ ተጠቃሽ ነው ። የገናና የጥበብ ባለቤት መሆኗን አክሱም እና ላሊበላ ዛሬም ቆመው ይመሰክሩላታል። በጥንት ጊዜ ወደብ የስልጣኔ ተጽዕኖ ፈጣሪነት መገለጫ በነበረበት ጊዜ ኢትዮጵያም ስሟ ጎልቶ ይነሳ ነበር። ወደብ ዓለምን እርስ በእርስ ከማስተሳሰር ባለፈ የግብይት የጀርባ አጥንት ሆኖ ሲያገለግል ቆይቷል፤ ዛሬም እያገለገለ ይገኛል። ሀገራት አዋጭ የንግድ ስትራቴጂ ቀይሰው የተለያዩ ወደቦችን የመጠቀም ልምዳቸው በታሪክ ውስጥ ጎልቶ የሚነሳ ነው። የንግድ ሥርዓታቸውን በወደብና በየብስ ከሚያከናውኑ የዓለም ሀገራት መካከል ደግሞ ኢትዮጵያ አንዷ ናት። የታሪክ ድርሳናት እንደሚያሳዩት ኢትዮጵያ በተለያዩ ዘመነ መንግስታት የተለያዩ ወደቦችን በባለቤትነት አስተዳድራለች። ከአክሱም ዘመነ መንግሥት ጀምሮ እስከ ደርግ መንግስት ድረስ አዱሊስ፣ አሰብ፣ ዘይላ፣ ምጽዋና ሌሎች ወደቦችን ለኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች ትገለገል ነበር። ይሕ የኢትዮጵያ የወደብ ባለቤትነት ታሪክ እስከ 1983 ዓ.ም ድረስ የዘለቀ እንደነበር በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሰቲ የታሪክ እና ቅርስ አስተዳደር ትምሕርት ክፍል መምሕር አጥናፉ ምትኩ ይናገራሉ። ወደብ ከኢኮኖሚያዊ ጥቅም ባሻገር ፖለቲካዊ እና ማኅበራዊ ፋይዳው ከፍተኛ እንደሆነም አውስተዋል።   በታሪክ ኩነት ውስጥ የተፈጠረ ሴራና ተንኮል ኢትዮጵያ የባሕር በር አልባ ሀገር እንድትሆን አድርጓታል። ይሕም ከሆነ ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ ተቆጥሯል። በዚሕም ኢትዮጵያ ለወደብ ኪራይ በየዓመቱ ብዙ ቢሊዮን ብር እየከፈለች የወጪ እና ገቢ ንግድን የማንቀሳቀስ እዳ ተጭኖባታል። ይሕም የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ወደ ኋላ ከሚጎትቱ ጉዳዮች አንዱ ሆኖ ዛሬ ድረስ ዘልቋል። የወደብ አገልግሎት ነጻነት ማጣት፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶች ዋጋ መጨመር፣ ማዳበሪያን ጨምሮ አስፈላጊ ግብአቶች መዘግየትና በወቅቱ አለመድረስ፣ በዚሕም የሰብል ልማት ስራዎች ላይ ችግሮች መስተዋል ከባሕር በር ባለቤትነት እጦት ጋር የመያያዝ እድላቸው ሰፊ ነው። እነዚሕ ችግሮች ደግሞ ተደማምረው ለኑሮ ውድነት መፈጠር አስተዋጾኦ ይኖራቸዋል ማለት ይቻላል። በታሪክ አጋጣሚ የተፈጠረው ስብራት እያስከተለ ያለው ጉዳት አሁን ላይ ለኢትዮጵያ የሕልውና ጉዳይ በመሆኑ በታሪካዊ ዳራ መሠረት መጠገን ያስፈልጋል። ለኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ከ130 ሚሊዮን ያሻቀበ የሕዝብ ቁጥር፣ የኢኮኖሚ ዕድገትና ሀገራዊ የቆዳ ስፋት ገፊ ምክንያቶች ከሚባሉት ውስጥ ይጠቀሳሉ። በሌላ በኩል ከዚሕ ቀደም የነበረው የሀገሪቱ ባሕር በር ባለቤትነት ማስረጃ ዛሬ ላይ አስቻይ ሁኔታን የሚፈጥር ነው። መንግሥት የጀመረው የባሕር በር ባለቤት የመሆን ጥያቄ በመሬት ተዘግቶ የመኖር ታሪክ እንዲያበቃ የሚያደርግና በዓለም አቀፍ ሕግ ተፈጥሮን በጋራ ተጠቅሞ የመልማት መብትን የሚያስጠብቅ መሆኑ እውን ነው። ለሦስት አስርት ዓመታት ታፍኖ የቆየው የቀይ ባሕር ባለቤትነት ጥያቄ የመንግስት ቁርጠኝነት እንዳለ ሆኖ ዜጎችም አጥብቀው በመያዝ መልስ እስኪያገኝ ድረስ መስራት ይጠበቃል። የሀገርና የሕዝብ የዘመናት ጥያቄ የሆነው የባሕር በር እስኪሳካ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ሥራ መሥራት ከሁሉም ኢትዮጵያዊ እንደሚጠበቅ መምሕር አጥናፉ ይገልጻሉ። ለኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤት መሆን የታሪኳና ዕድገቷ ወጌሻ ነው ያሉት መምሕር አጥናፉ ኢትዮጵያ የባሕር በር ለመጠቀም የሚያስችላት ታሪካዊ መብት አላት። ይሕን ታሪካዊ መብቷን የምታረጋግጥበት ትልቁ መሣሪያ ደግሞ ያላት ጠንካራ የዲፕሎማቲክ አቅሟ ነው። ከዓለም ሀገራት ጋር ያላት መልካም ግንኙነት ተናግሮ ለማሳመን እውነታን ለመግለጽ የሚያስችላት ነው። ይሕንንም በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በዓለም ፊት አረጋግጣለች። ይሕን የሕዳሴ ድል በቀይ ባሕር ላይ የማትደግምበት ምንም ምክንያት አይኖርም። በተለይ ኢትዮጵያ ያላት የጋራ ተጠቃሚነት መርሕ በዓለም ላይ ተቀባይነት ያለውን ሀሳብ ይዛ እንድትቀርብ እያስቻላት ይገኛል። ለጎረቤት ሀገራት ቅድሚያ የሚሰጠው የውጭ ግንኙነት ፖሊሲዋ ተፈጥሮን ተባብሮ በማልማት እንጠቀም የሚል መሠረት ያለው ነው። መምሕር ይስሐቅ ንጉሤ በሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሰቲ የምጣኔ ሀብት መምሕር ሲሆኑ የባሕር በር ጉዳይ የኢኮኖሚ ዕድገት ማጠንጠኛ ሆኖ የሚያገለግል መሆኑን አንስተው ኢትዮጵያ የባሕር በር ማጣቷ በፈጣን ዕድገቷ ላይ መሰናክል ሆኖ መዝለቁን ተናግረዋል።   በተለይ የዓለም ሀገራት ከፍተኛው የንግድ፣ የኢኮኖሚና ሀብት እንቅስቃሴ የሚታይበት እና የሀገራት የንግድ ልውውጥ የሚካሄድበት የቀይ ባሕር ቀጠና ላይ ያለውን አብሮ የመስራትና ከማደግ ዕድል ኢትዮጵያ ያለአግባብ መገለሏን ያነሳሉ።ይሕም በሀገሪቱ ምጣኔ ሀብታዊ ዕድገትና በሌሎች ላይ ያሳደረው አሉታዊ ተጽዕኖ ከፍተኛ እንደሆነ ነው ያገለጹት። የባሕር በር ጥያቄ የምጣኔ ሀብት ዕድገትን በማሳለጥ ሀገሪቱ ከልመና ለመውጣት ያላትን ዕድል እንድትወስን ያስችላታል የሚሉት መምሕሩ ፤ለስኬቱም የተጀመረውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ማጠናከር እንደሚገባም ነው የገለጹት። እንደ መምሕሩ ገለጻ ከዓለም አቀፍ መርሆችና ስምምነቶች እንዲሁም ካለን መልከአ ምድራዊ አቀማመጥና ታሪክ አንጻር ለኢትዮጵያ የባሕር በር ተገቢ ነው። ይሕ እንዲሳካም መንግስት ካሳየው ቁርጠኝነት በተጨማሪ ሁሉም በተቀናጀ መንገድ የሚያደርገውን ጥረት ማጠናከር ይኖርበታል። መንግስት የዘመናት የትውልዱ ጥያቄ ሆኖ የቆየውን የባሕር በር ጉዳይ በግልጽና በይፋ መረጃ በመስጠት ዓለም አቀፍ አጀንዳ እንዲሆንም ጭምር እያደረገ ያለውን ጥረትንም አድንቀዋል። ታሪክ በኩነቶች መካከል መጥፎም መልካም ሆኖ ያልፋል። በታሪክ የባሕር በር ባለቤትነታችን የገጠመውን ስብራት ለመጠገን የሚያስችል ወጌሻ ያስፈልጋል። በታሪክ ሂደት መልካሙ ወደ መጥፎ ሁኔታ እንደሚቀየር ሁሉ የተበላሸን ወደ መልካም የመቀየር ዕጣ ፈንታ ያለው የዛሬው ትውልድ ላይ ነው። ለእዚሕ ደግሞ ትውልዱ በሕዳሴው ግድብ ከመንግስት ጎን ሆኖ ያሳየውን አንድነትና ሕብረት በባሕር በርም መድገም አለበት። ታሪካዊ ዳራን፣ ዲፕሎማሲን፣ ሀገራዊ ነባራዊ ሁኔታና ሕግን ተከትሎ በአብሮነት ከተሰራ ያኔ የተበላሸው ይቃናል፤ ያጣነውን እናገኛለን። "እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል" ዓይነት እንስሳዊ ግብር በ21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሊሰማ አይገባም፤ መሰማትም አይኖርበትም። ኢትዮጵያ ብታደግ ለቀጣናው ኩራት፤ ለአፍሪካም ልዕልና እንጂ ጥፋት የሚያስከትል እንዳልሆነ መገንዘብና የትብብር ልማትና ዕድገትን ባሕል ማድረግ ሊለመድ ይገባል። ሰላም!
የዳሰነቾች ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴ ''ጀለባ''
Oct 30, 2025 1163
የዳሰነች ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴ ''ጀለባ'' (በጣፋጩ ሰለሞን ከጂንካ ኢዜአ ቅርንጫፍ) ዳሰነቾች በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በደቡብ ኦሞ ዞን ውስጥ ከሚገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ጋር በአብሮነት ተጎዳኝተው ይኖራሉ። የብሔረሰቡ አባላት ዋነኛ መተዳደሪያ ከብት እርባታ ሲሆን፤ ከከብት እርባታው ጐን ለጐን በዝቅተኛ ደረጃ በግብርናና በዓሳ ማስገር ስራ ይተዳደራሉ፡፡ ዳሰነቾች በሰሜን ከሐመር፣ በደቡብ ከኬኒያ፣ በምስራቅ ከቦረና በስተ ምዕራብ ደግሞ ከኛንጋቶም ማህበረሰብ ተጎራብተው ይኖራሉ። ዳሰነቾች ከኩሽቲክ የቋንቋ ነገድ የሚመዘዝ ''አፍ ዳሰነች'' የተሰኘ የመግባቢያ ቋንቋም አላቸው። ዳሰነቾች የተለየ የአለባበስ፣ የአጋጌጥ፣ የቤት አሰራር እና የባህላዊ የሙዚቃ ስልተ ምትን ጨምሮ አስደማሚ ባህሎች እና ማራኪ የመልክዓ ምድር አቀማመጥን የታደሉ ናቸው። ዳሰነቾች ከሚታወቁባቸው አስደማሚ ባህሎች ውስጥ አንዱ የሆነው አለመግባባቶችን በውይይት የሚፈቱበት የ''ጀለባ''ስርዓት ተጠቃሽ ነው። ይህ ስርዓት ግጭቱ ቂምና ቁርሾ በማይሻገርበት መልኩ በዘላቂነት የማስወገድ አቅም ያለው ሲሆን የማይናወጥ ሰላምና ወንድማዊ ትስስር እንዲጠናከርም ሚናው የጎላ ነው። ዕሴቱ የዳሰነቾች የአኗኗር ቁመና የሚለካበትና የሚመዘንበት መጻኢንም የሚተለምበትም ጭምር ነው። ስለሆነም በዳሰነቾች ዘንድ ቂም መያዝ አሎሎ ተሸክሞ እንደመዞር ይቆጠራል ነው የሚባለው። የባህሉ ተመራማሪ ሊዮን አርሎት 'ጀለባ'' የተሰኘው ባህላዊ ዳኝነት ከአካባቢው ሰላም አልፎ ለቀጠናው ወንድማማችነት መጠናከር ትልቅ ሚና ያለው የፍትህ ስርዓት መሆኑን ያነሳሉ። በ''በጀለባ'' ስርዓት ባህላዊ የዳኝነት አሰጣጥ እርከኖች እንዳሉ ጠቅሰው፥ አለመግባባቶች ሲፈጠሩ ''ኖሞ'' የተሰኙ ሽማግሌዎች ወደ ስፍራው በማቅናት የግጭቱን መንስኤ በማጣራት ''ቶሎል'' ለተሰኙ ሌሎች ሽማግሌዎች የሚያሳውቁበት አሰራርም አላቸው። እንደ ግጭቱ ቅለትና ክብደት ''ቶሎል'' በተሰኙ ሽማግሌዎች ተለይቶ ቀለል ያለው ''ካባና'' በተሰኙ ዳኞች ውሳኔ የሚሰጥ ሲሆን፥ ጉዳዩ ከበድ ያለ ከሆነ ደግሞ የመጨረሻው ውሳኔ ''አራ'' በተሰኙ ዳኞች ይሰጣል። ከነፍስ ማጥፋት በስተቀር ሁሉም ውሳኔዎች ''አራ'' በተሰኙ ዳኞች እልባት ያገኛሉ። የነፍስ ማጥፋት ወንጀል ሲከሰት ግን ጉዳዩን ለመንግሥት አሳልፎ በመስጠት ጉዳዩ በፍርድ ቤት ውሳኔ እንዲያገኝ ይደረጋል ። ነፍስ ያጠፋው ሰው የእርምት ጊዜውን አጠናቆ ማህበረሰቡን ለመቀላቀል ሲወስን ባህላዊ የዕርቅ ስነ-ስርዓት ተዘጋጅቶ በዳይና ተበዳይ ይቅር የሚባባሉበትም ስርዓት እንዳለ የባህሉ ተመራማሪ ይናገራሉ።   በዳሰነቾች ባህል ልዩነቶች ሰላማዊ በሆነ መንገድ በዘላቂነት መንገድ የመፍታት ዘመናትን የተሻገረ ድንቅ ዕሴት መኖሩን የሚያነሱት የብሔረሰቡ አባል አሸቴ ነካሲያ፤ “በዳሰነች ብሔረሰብ ቂም መያዝ አሎሎ ተሸክሞ እንደመዞር ይቆጠራል'' ይላሉ። በዳሰነቾች አለመግባባቶች በውይይት የሚፈቱበት ስርዓት እንዳለ ጠቅሰው፥ ''ናብ'' በተሰኘው የዳኝነት ስፍራ አለመግባባቶች ውለው ሳያድሩ እልባት ያገኛሉ ብለዋል። ሌላው የብሔረሰቡ አባል ሎቶያቡስ ሎኪሰሬሬ በበኩላቸው የባህል መሪዎች የተጣላን ማስታረቅ፣ ትውልዱን የመግራትና በስነ-ምግባር የማነፅ ኃላፊነት እንዳላቸው ጠቅሰዋል። ''ማንም ሰው ከባህል መሪዎች ትዕዛዝ አያፈነግጥም'' የሚሉት አቶ ሎቶያቡስ፥ ሁሉም እርስ በእርስ በመከባበር እና ችግሮች ሲኖሩ በውይይት በመፍታት አብሮነቱን ያጠናክራል ብለዋል።   ወጣቱ ለባህል መሪዎች ታዛዥ ነው የሚሉት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ የብሔረሰቡ አባል ሎሲያ ሎብቻ ወጣቶች ለአካባቢው ሰላም ዘብ እንዲቆሙ፣ ከአጎራባች ህዝቦች ጋር በፍቅር እንዲኖሩ በማስተማር ወጣቱን በስነ-ምግባር የማነፅ ስራ እንደሚሰሩም ተናግረዋል። የዳሰነች ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታደለ ሀቴ በበኩላቸው የዳሰነች ህዝብ ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴ ከወረዳው አልፎ ለቀጠናው ሰላም ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክቷል ብለዋል። የብሔረሰቡ ባህላዊ የሽምግልና ስርዓት ትውልዱን በመግራት በስነ- ምግባር የታነፀ ዜጋ እንዲፈጠር እንዳደረገም አስረድተዋል።   የጂንካ ዩኒቨርሲቲ የሶሻል አንትሮፖሎጂ መምህርና ተመራማሪ አጎናፍር ሰለሞን፤ ባህላዊ የዳኝነት ስርዓቶች ለዘመናዊው የፍትህ ስርዓት መጠናከር ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ብለዋል። ባህላዊ የግጭት አፈታት ሥርዓቶች ቅጣት በመጣል ጥፋተኝነት እንዲሰማ የሚያደርጉ ሳይሆኑ፤ እውነተኛ ይቅርታን የሚያሰፍኑና ለአብሮነት የሚበጁ ዕንቁ ባህሎች እንደሆኑም አብራርተዋል።   ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎቹ በግለሰብ ተጠቃሚነት ላይ ሳይሆን በማህበረሰብ ተጠቃሚነት ላይ ትኩረት የሚያደርጉ በመሆናቸው ከዘመናዊው የፍትህ ስርዓት በይበልጥ ለአብሮነት መጠናከር አስተዋጽኦ እንዳላቸውም ገልጸዋል። ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎቹም ለሀገራዊ መግባባት ሚናቸው የላቀ በመሆኑ፥ እሴቶቹ ተጠብቀው፣ ለምተውና ጎልብተው ጥቅም ላይ እንዲውሉ መስራት እንደሚገባም መክረዋል። ሀገራችን ቂምና ቁርሾን የወለዱ ያለመግባባቶች በዘላቂነት በሰለጠነና ሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በማቋቋም ሁሉንም ያሳተፈ ስራ እየሰራች እንደሆነ ያነሱት መምህርና ተመራማሪው አጎናፍር ሰለሞን ዕሴቶቹ በማህበረሰቡ ዘንድ ካላቸው ተቀባይነት እንዲሁም ሀገራዊ የምክክር ሂደቱን ከማገዝ አንጻር ጉልህ ሚና ስለሚኖራቸው መጠቀም እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
''ቦር ተራራ'' የየሞች የፈውስ ምድር 
Oct 27, 2025 626
(በእንዳልካቸው ደሳለኝ ከወልቂጤ ኢዜአ ቅርንጫፍ) የም ዞን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውስጥ ይገኛል። በዞኑ የቦር ተራራ ዋነኛው የመድኃኒት እጽዋት መገኛ እና ምንጭ በመሆኑ የሞች በየዓመቱ ጥቅምት ወርን ጠብቀው በ17ኛው ቀን ከዚህ ተራራ በህብር ሆነው የመድኃኒት እጽዋት ለቀማ ስነ-ስርዓት ያካሂዳሉ፤ ይሰባስባሉም ። የቀደምት የየም አባቶችና እናቶችን በማሳተፍ የሚከወነው የመድኃኒት እጽዋት ለቀማ ከባህር ጠለል በላይ 2 ሺህ 939 ሜትር ከፍታ ላይ በሚገኘው ቦር ተራራ ላይ ነው። በዚህ ተራራ ላይ በየዓመቱ ጥቅምት 17 ቀን የሞች ለዓመት የሚያገለግላቸውን የመድኃኒት እጽዋት ይለቅማሉ። ተግባሩንም አዋቂዎች በጋራ ሰብሰብ ብለው ለመድኃኒት የሚውለውን ቅጠል በጥሰው፣ ስር ምሰው፣ አስሰውና መርጠው ይሰበስባሉ። ይህም የመድኃኒት እጽዋት ለቀማ ስርዓት "ሳሞ ኤታ" ተብሎ ይጠራል ። አያምጣውና ህመም ሲከሰት ታማሚውን ሰው ወይም እንስሳን ከበሽታው ለመፈወስ የተዘጋጀው ባህላዊ መድሃኒት በባህላዊ ሃኪም ትዕዛዝ መሰረት በህመሙ ልክ ይታዘዝለታል። መድሃኒቱን ለመጠቀምም የጠቢባን አባቶችን ፈለግ ተከትሎ መፈፀም የግድ ይላል። የሞች አጅግ አስገራሚ እና አስደናቂ የሆኑ የበርካታ አገር በቀል ዕውቀቶች ባለቤት ናቸው ካስባሏቸው እሴቶች መካከል ይህ ለየት ያለው ክዋኔያቸው አንዱ ነው፡፡ አባቶች ታዳጊና ወጣቶችን አስከትለው ወደ ቦር ተራራ በመውጣት የሚፈፅሙት ባህላዊ ክዋኔ በመሆኑም ከትውልድ ወደ ትውልድ ቅብብሎሹን ጠብቆ እስከ አሁን እንዲዘልቅ እድርገውታል።   በየሞች ዘንድ የባህላዊ መድኃኒት አዋቂዎች ከሚባሉት መካከል አንዱ አቶ ጌታቸው ሃይለማርያም፤ የመድኃኒት ዕፅዋት ለቀማ ልምድን የቀሰሙት ከአባታቸው መሆኑን በመግለፅ አያታቸው ከቅድመ አያቶቻቸው በመውረስ እዚህ እንዳደረሱት ይናገራሉ። የቦር ተራራ ለመድሃኒት ዕፅዋት ለቀማው የተመረጠበትን ምክንያት ሲያስረዱም ቦታው ተራራ በመሆኑ ማንም ያልደረሰባቸው የተለያዩ እፅዋትን ለማግኘት አመቺ ከመሆኑ ጋር ያያይዙታል። በሌላም በኩል ጠዋት ፀሐይ ስትወጣ መጀመሪያ የምታገኘው ተራራውን በመሆኑና ክረምቱ አልፎ ጥቅምት ሲገባ የተለያዩ ቅጠላ ቅጠሎችን በብዛት እና በዓይነት ለማግኘት ተመራጭ ወቅት መሆኑም ቦታው የተመረጠበት ሌላኛው ምክንያት ነው ብለዋል። በጥቅምት 17 ለመድኃኒትነት የሚያገለግለው ዕፅዋት ቅጠልም በየፈርጁ ተለቅሞ እና ተቀምሞ ይቀመጣል ሲሉም አስረድተዋል። የተዘጋጀው ባህላዊ መድኃኒትም ለሰው ልጆችና ለቤት እንስሳት ያገለግላል ሲሉም አስረድተዋል፡፡ ይኸው በዚህ ቀን የተለቀመው የመድኃኒት ዕፅዋት ከዚህኛው ጥቅምት 17 እስከሚቀጥለው ዓመት ጥቅምት 17 ድረስ እንደሚያገለግልም አቶ ጌታቸው አስረድተዋል፡፡ የባህል መድኃኒት ሰብሳቢዎች እና ተጠቃሚዎች ጊዜውን ጠብቀው ከተለያዩ ቦታዎች ወደ ቦር ተራራ እንደሚመጡ የሚገልጹት የባህል መድኃኒት አዋቂው ዛሬ ዛሬ እሳቸውን ጨምሮ መድኃኒት ቤቶችን በመክፈት ፈዋሽነታቸው የተረጋገጡ የባህል መድኃኒቶችን በመሸጥ ኑሯቸውን እየመሩ የሚገኙ አያሌ የአካባቢው ነዋሪዎች እንዳሉም ይናገራሉ። ሌላኛው የባህል መድኃኒት አዋቂው አቶ ወልደመስቀል ጆርጋ በበኩላቸው በየሞች ዘንድ የተዘጋጀው የመድኃኒት ዕፅዋት ጥቅም ላይ የሚውለው ህመም ሲያጋጥም ብቻ ሳይሆን በሽታን አስቀድሞ ለመከላከል መሆኑን ጠቁመው መድኃኒቶቹም ብቻቸውን እንዲሁም ከምግብ ጋር በመመገብ ለጥቅም እንደሚውሉም አንስተዋል። የየም ምድር የበርካታ የመድኃኒት ዕፅዋቶች መገኛ አካባቢ " የፈውስ ምድር " ነው የሚሉት ደግሞ በየም ባህላዊ መድኃኒት ዙሪያ ጥናት ያደረጉት በጅማ ዩኒቨርሲቲ የፎክሎር መምህር እና ተመራማሪ ለማ ንጋቱ (ዶ/ር) ናቸው። ከየሞች አያሌ የባህል ዕሴቶች መካከል የባህል መድኃኒት ለቀማና ቅመማ አንዱና ዋነኛው የሀገር በቀል እውቀት ማሳያ መሆኑን ገልፀው የመድኃኒት ዕፅዋት ለቀማ ስነ-ስርዓቱ ከጥንት ጀምሮ ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተሸጋገረ ዛሬ ላይ የደረሰ እንደሆነም ያስረዳሉ፡፡   ማህበረሰቡ የራሱንም ሆነ የእንስሳትን ጤና የመጠበቅ የቆየ ባህል ያለው መሆኑን በጥናት መረጋገጡን ጠቅሰው የባህላዊ መድኃኒት ለቀማው ከሊቅ እስከ ደቂቅ የሚሳተፉበት ዓመታዊ ክዋኔ እንደሆነም ተናግረዋል፡፡ ሌላው ገራሚው ነገር ይላሉ አጥኚው ታላላቆች ታናናሾቻቸውን አስከትለው የለቀማ ሂደቱን የሚያስረዱበት መንገድ ደግሞ ስርዓቱ ለመጪው ትውልድ እንዲተላለፍ የሚያስችል ትውልድ ተሻጋሪ የሀገር በቀል እውቀት ሽግግር ስርዓት ማሳያ እንደሆነም ነው የገለጹት። በዚህም ሂደት የሚነገሩ ስነ-ቃሎች መሞጋገስ፣ ጭፈራና ደስታ ይስተናገድባቸዋል። ይህም ማህበራዊ ትስስርን ይበልጥ የሚጠናክሩበትን ሁነት የሚፈጥር ስርዓት ነው። የየም ዞን ባህል እና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ አቶ መስፍን ሞጋ በበኩላቸው የቦር ተራራ የመጀመሪያውን የማለዳ የፀሐይ ጎህ የሚፈነጥቅበት የንጋት ብርሃን ቀድሞ የሚያገኝ በመሆኑ፥ በዚህ አካባቢ የሚገኙ እጽዋት በሽታን የመከላከልና ፈዋሽነታቸው ከፍተኛ ነው ተብሎ ስለሚታመን ለዚህ ክዋኔ ቦታው መመረጡን ነው የሚገልፁት። ለዚህም ነው የሞች ይህንን ስፍራ ከሌሎች ቦታዎች አስበልጠው የሚወዱት፤ በየዓመቱም ጥቅምት 17 ቀን ወደ እዚህ ስፍራ በማቅናት ለዓመት ፍጆታ የሚያገለግላቸውን መድኃኒትም ይሰበስቡበታል ብለዋል። ጥቅምት 17 በየም ዘንድ ለየት የሚያደርገው ሌላው የመድሃኒት ዕፅዋት ለመልቀም እና ለመጠቀም ብቻ ሳይሆን የለቀማውን ትዕይንት ለመመልከት የሚመጡ ቱሪስቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመሩ መምጣታቸው ሌላው ትልቁ ትሩፋት ነው ይላሉ። የመድኃኒት ዕፅዋት ለቀማው ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የሚሳተፉበት በመሆኑ፥ ለአብሮነት እና ሃገር በቀል እውቀት ለመቅሰም ከፍተኛ ሚና እንዳለውም ነው አቶ መስፍን የገለፁት።    
የአፍሪካ የግብርና፣ ውሃ እና ከባቢ አየር አጀንዳ፤ እድሎች እና ፈተናዎች
Oct 20, 2025 723
አፍሪካ ዘላቂ ልማትን ለማሳካትና እንድትበለጽግ የጀመረችው ጉዞ ወሳኝ መዕራፍ ላይ ይገኛል። የአህጉሪቱን የመለወጥ ትልም ባሏት እምቅ ተፈጥሯዊ ጸጋዎች ላይ የተመረኮዘ ነው። ተዝቆ የማያልቀው የአፍሪካ ብዝሃ ሀብት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግና አይበገሬ አቅም መገባንት የሚያስችሏትም ጭምር ናቸው። ግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የውሃ ሀብቶቿ እና ብዝሃ ከባቢ የአየር ንብረቷ ከሀብቶቿ መካከል ይጠቀሳሉ። ግብርና አሁንም የአፍሪካ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ነው። ዘርፉ ለአህጉሪቱ 35 በመቶ የሚጠጋ አጠቃላይ ጥቅል ሀገራዊ ምርት(ጂዲፒ) አስተዋጽኦ ያደርጋል። 60 በመቶ ህዝብም በግብርና ስራ እንደሚተዳደር የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የልማት ፕሮግራም (ካዳፕ) ሰነድ ያሳያል። ከዚህም ውስጥ አብዛኞቹ አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮች ናቸው።   ሴቶች በግብርናው ዘርፍ ካለው የሰው ኃይል የ50 በመቶ ድርሻው ይወስዳሉ። የአፍሪካ ህዝብ 60 በመቶ ድርሻ የያዘው ወጣት በግብርና ንግድ፣ እሴት መጨመርና የኢኖቬሽን ስራዎች ያለው ተሳትፎ እያደገ መጥቷል። የዓለም 60 በመቶ ያልለማ መሬት ያለው በአፍሪካ ነው። ሰፊ የውሃ ሀብቶችና እያደገ ያመጣው ብሉ ኢኮኖሚ(የባህር እና ሌሎች የውሃ ሀብቶች) ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ እድገትን የሚያረጋግጡ ናቸው። የመሰረተ ልማቶች ተደራሽነት ማደግ፣ ቀጣናዊ የእሴት ሰንሰለቶችና ኢኖቬሽንን የተመረኮዙ የፋይናንስ አማራጮችን መስፋት ግብርናን የምግብ ምንጭ ብቻ ሳይሆን ለኢንዱስትሪ ልማት፣ የስራ ዕድል ፈጠራ እና ንግድ መሳለጥ ትልቅ አቅም መሆን ይችላል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና በግብርና ምርቶችና አገልግሎቶች ያለውን አህጉራዊ የእርስ በእርስ የንግድ ልውውጥ በማሳደግ ረገድ ትልቅ ዕድል ይዞ የመጣ ነው። የንግድ ቀጣናውን በሚገባ መጠቀም ከተቻለ እ.አ.አ በ2030 የግብርና ንግድ ልውውጡን በ30 በመቶ ማሳደግ እንደሚቻል ጥናቶች ያመለክታሉ። ግብርናው የተጠቀሱት ጥንካሬዎች ያሉት ቢሆንም ረጅም ጊዜ የዘለቁ መዋቅራዊ ፈተናዎች አብረውት ዘልቀዋል። የግብርና ምርቶች ላይ የሚፈለገውን ያህል እሴት አለመጨመር፣ የቴክኖሎጂ አጠቀቃምና የምርታማነት ውስንነት፣ የመሰረተ ልማቶች እና ሎጅስቲክስ በበቂ ሁኔታ አለመሟላት፣ ተቋማዊና አስተዳደራዊ ክፍተቶች ከአየር ንብረት ለውጥና ሌሎች ተፈጥሯዊ አደጋዎች እንዲሁም እያደገ ከመጣው ህዝብ ጋር ተዳምሮ ግብርናውን እየፈተነው ይገኛል።   ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት የአፍሪካ የግብርና ትራንስፎርሜሽን አጀንዳ ማጠንጠኛ የሆነው ጉዳይ የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት(ካዳፕ) ነው። እ.አ.አ በ2003 የአፍሪካ ህብረት በሞዛምቢክ ባደረገው ስብሰባ የግብርና የምግብ ዋስትና ድንጋጌን አጽድቋል። ይህ ማዕቀፍ የማፑቶ ድንጋጌ ስያሜን በማግኘት የካዳፕ ትግበራ በይፋ እንዲጀመር አድርጓል። የማፑቶ ድንጋጌ እ.አ.አ በ2014 በማላቦ ድንጋጌ (ከእ.አ.አ 2014 እስከ 2025 የተተገበረ) በአዲስ መልክ የታደሰ ሲሆን የተለያዩ ቃል ኪዳኖችን በውስጡ ይዟል። ይህም በካዳፕ አማካኝነት የአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት ከአጠቃላይ ዓመታዊ ጥቅል ምርታቸው(ጂዲፒ) ቢያንስ ስድስት በመቶውን ለግብርናው ዘርፍ እንደሚመድቡና በየሀገራቱ በዘርፉ በየዓመቱ በአማካይ ስድስት በመቶ እድገትን የማሳካት ግብ አለው። ረሃብን ማጥፋት፣ ድህነትን በግማሽ መቀነስ፣ የማይበገር አቅም መገንባትና የጋራ ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ሌሎች ግቦች ናቸው። ካዳፕ የአፍሪካ ሀገራት በስርዓተ ምግብ ያላቸውን ኢንቨስተመንት በማሳደግ፣ በአፍሪካ የእርስ በእርስ የግብርና ንግድን በማሳደግና የፖሊሲ መሰናሰልን በመፍጠር ቁልፍ ሚና ተወጥቷል። ይሁንና የተመዘገቡት ውጤቶች ያልተመጣጠነ ልዩነት የሚታይባቸው ናቸው። የ2023 የካዳፕ የግምገማ ሪፖርት እንደሚያሳየው የአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት የማላቦ ግቦችን ማሳደግ የሚያስችል መንገድ ላይ እንዳልሆኑ ያስቀምጣል። ይሁንና 26 ሀገራት በተቀመጡ ግቦች መመዘኛ መሻሻል እንዳሳዩ ይገልጻል። ኢትዮጵያ፣ ብሩንዲ፣ ካሜሮን፣ ግብጽ፣ ማሊ፣ ጋና እና ጋምቢያ የተሻለ አፈጻጸም ካላቸው ሀገራት መካከል ይጠቀሳሉ። አብዛኞቹ ሀገራት በግብርና ኢንቨስትመንት፣ ምርታማነት እና የፖሊሲ ትግበራ ላይ ፈተናዎች እንዳሉበት ሪፖርቱ አመልክቷል። ሀገራት የሰነዱን ትግበራ ማፋጠንና ተቋማዊ ቅንጅትን ማጠናከር እንደሚገባቸው አሳስቧል።   የማላቦ ድንጋጌ ወደ መገባደዱ ላይ የሚገኝ ሲሆን የካዳፕ ቀጣዩ ምዕራፍ የካምፓላ ድንጋጌ ነው። ይህ የትግበራ ምዕራፍ ከእ.አ.አ 2026 እስከ 2035 የሚቆይ ነው። የካምፓላ ድንጋጌ ከማፑቶ እና ማላቦ ድንጋጌዎች ትምህርቶችን በመውሰድ የግብናውን እድገት ማላቅ ግቡ አድርጎ ይዟል። የካምፓላ አጀንዳ ኢኖቬሽን፣ ዲጂታላይዜሽን፣ አረንጓዴ እድገት እና አይበገሬነት ያላቸውን ሚና በማንሳት መስኮቹ ስርዓተ ምግብን ዘላቂና አካታች የማድረግ ግብን ማሳካት እንደሚያስችሉ አመልክቷል። በዚህ ማዕቀፍ እ.አ.አ 2050 2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ህዝብ ይኖራታል ተብሎ የሚጠበቀውን አፍሪካን በራስ አቅም የመመገብ ውጥን የያዘ ነው። ይሁንና የግብርና ምርታማነት ከዓለም አቀፍ አማካይ የምርታማነት ምጣኔ አንጻር ሲታይ አሁንም ወደ ኋላ ቀረት ያለ ነው። ይህም አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮች የተገደበ የፋይናንስ አቅርቦት ማግኘታቸው እንዲሁም የቴክኖሎጂ ተጠቃሚነትና የገበያ ትስስር እንዲፈጠርላቸው አለመደረጉ የችግሩ አብይ መንስኤ ሆኖ ይጠቀሳል። የአየር ንብረት ለውጥ ፈተናዎችና የከባቢ አየር ብክለት ፈተናዎቹ እንዲበረቱ አድርጓል። ዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ የበይነ መንግስታት ፓናል(IPCC) አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ማጣጣሚያ እርምጃዎችን በፍጥነት ካልወሰደች እ.አ.አ በ2050 የግብርና ምርታማነቷ ከ20 እስከ 30 በመቶ ሊቀንስ እንደሚችል ገምቷል። ከ250 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ አፍሪካውያን ደህንነቱ ያልተረጋገጠ እና ንጽህናው ያልተጠበቀ የውሃ አቅርቦት ፈተና ውስጥ ይገኛሉ። በህዝብ ቁጥር መጨመር፣ በከተሜነትና ኢንዱስትሪ መስፋፋት ምክንያት ንጹህ የውሃ አቅርቦትን የማግኘት ጉዳይ የበለጠ ሊስፋ እንደሚችል ተመላክቷል። የአፍሪካ ህብረት የተቀመጡ ግቦች እንዲሳኩና ፈተናዎች ዘላቂ መፍትሄ እንዲያገኙ ለአባል ሀገራት የፋይናንስ እና የቴክኒክ ድጋፎችን እያደረገ ይገኛል። የህብረቱ የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ ከባቢ አየር የስራ ክፍሉ(DARBE) አማካኝነት የአፍሪካን ፖሊሲዎች፣ ፕሮግራሞችና ኢኒሼቲቮች የተናበቡና የጋራ ግብ ያላቸው እንዲሆኑ ክትትልና ድጋፍ ያደርጋል። የአቅም ግንባታ፣ የቴክኒክ እና የፖሊሲ ድጋፍም የሚያደርግ ሲሆን ብሄራዊ እቅዶች ከአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ሰነዶችና የአጋርነት ማዕቀፎች ጋር የተጣጠሙ መሆናቸውን ያረጋገጣል። የስራ ክፍሉ ከቀጣናዊ የኢኮኖሚ ማህበረሰቦች፣ የግሉ ዘርፍና የልማት አጋሮች ጋር አጋርነቶችን የማጠናከር ስራ ያከናውናል። ግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ አስተዳደር፣ የአየር ንብረት ለውጥ አይበገሬነት እንዲሁም የተፈጥሮ እና የብሉ ኢኮኖሚ ሀብቶች በዘላቂነት መጠቀም ላይ የተቀናጁ አሰራሮችን መፍጠር ላይም ይሰራል። የዘርፉ አጠቃላይ ስራዎች አካል የሆነው ስድስተኛው የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ጥቅምት 11 ቀን 2018 ዓ.ም በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ መካሄድ ይጀምራል። በስብሰባው ላይ ሚኒስትሮች፣ ባለሙያዎችና የልማት አጋሮች ይሳተፋሉ። የአፍሪካ የግብርና ኢኒሼቲቮች አፈጻጸም መገምገምና ዘርፉ ሁሉን አቀፍና ዘላቂ ማድረግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ መምከር የስብሰባው አላማ ነው። እ.አ.አ በ2023 በአዲስ አበባ የተካሄደውን አምስተኛው የልዩ ኮሚቴ ስብሰባ ውጤቶች ግምገማ ይደረጋል። የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት ፕሮግራም(ካዳፕ) የማላቦ ድንጋጌ(ከእ.አ.አ 2014 እስከ 2025) ስኬቶች እና የካዳፕ የካምፓላ ድንጋጌ (ከእ.አ.አ 2026 እስከ 2035) አፈጻጸም ላይ ውይይት ይካሄዳል። የስርዓተ ምግብን ማጠናከር፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ምርታማነት ስርዓት መዘርጋት፣ የበካይ ጋዞችን ልህቀት መቀነስና ዘላቂ የውሃና የተፈጥሮ ሀብቶች አስተዳደርን ማጠናከር ሌሎች የምክክር አጀንዳዎች ናቸው። በአፍሪካ በገጠር አካባቢ የሚኖሩ ዜጎችን ኑሮ በማሻሻል ዘላቂ እድገትን ማምጣት በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ምክረ ሀሳቦች ይቀርባሉ። ውይይቱ እ.አ.አ በ2026 በአዲስ አበባ የሚካሄዱትን የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባና የህብረቱ የመሪዎች ጉባኤ የሚሆኑ አጀንዳዎችን እንደሚያዘጋጅ ተመላክቷል። የአፍሪካ ህብረት ግብርና፣ የገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር አጀንዳ 2063 ለማሳካት ቁልፍ ሚና የሚጫወቱ ዘርፎች መሆናቸውን አመልክቷል። ህብረቱ የግብርና እና የገጠር ልማት የበለጠ ማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝም አመልክቷል። የህብረቱ አባል ሀገራት የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት ፕሮግራምን በተጠናከረ ሁኔታ እንዲተገብሩም ጥሪ አቅርቧል። ስድስተኛው የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ ጥቅምት 11 እና 12 እንዲሁም ጥቅምት 14 በሚኒስትሮች ደረጃ እንደሚያከናውን ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። አፍሪካ ወደ ዘላቂ ግብርና፣ የገጠር ልማት፣ ውሃ አስተዳደር እና አካባቢ ጥበቃ እያደረገች ያለው ጉዞ አንገብጋቢ አጀንዳና ሽግግሩን ለማፋጠን ወሳኝ ሚና አለው። አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የፋይናንስ ማነቆ፣ መሰረተ ልማቶች እና የፖሊሲ የመፈጸም አቅም ውስንነትን ጨምሮ የተለያዩ ፈተናዎች ቢኖሩባትም እድሎቿ ፈርጀ ብዙ ናቸው። በርካታ ያልለማ መሬት፣ ሰፊ የውሃ ሀብት፣ ወጣቶች እና የብሉ ኢኮኖሚ ሀብቶች በአፍሪካ ዘላቂ የግብርና እድገት ለማረጋገጥና ሁሉን አቀፍ ስርዓተ ምግብ ለመገንባት የሚያስችል ነው። ለአርሶ አደሮች በቂ የፋይናንስ አቅርቦት ተደራሽ ማድረግን ጨምሮ አቅማቸውን መገንባት ቁልፍ ጉዳይ ነው። ሀገራት ብሄራዊ ፖሊሲዎቻቸውን ከአህጉራዊ ማዕቀፎች ጋር ማጣጣም ይኖርባቸዋል። ግቦችን ለማሳካት የተቀናጀ የባለድርሻ አካላት የአሰራር ማዕቀፍ መዘርጋት ይገባል። የተፈጥሮ ሀብትን በሚገባ መጠቀም፣ በኢኖቬሽን ላይ መዋዕለ ንዋይን ፈሰስ ማድረግና አህጉራዊ ትብብርን ማጠናከር የምግብ ዋስትናዋን ያረጋገጠች፣ አረንጓዴ እና የበለጸገች አህጉር መገንባት ይቻላል።
ኢሬቻ ለሁለንተናዊ ሀገራዊ ማንሰራራት!
Oct 3, 2025 1227
ኢሬቻ የምስጋና በዓል ነው፤ ሰዎች በክረምት ወቅት ከሚከሰት መለያየትና መራራቅ በኋላ ዳግም የሚገናኙበት፣ በአብሮነት ብርሃን ለማየት ያበቃቸውን ፈጣሪ የሚያመሰግኑበት ዕለት ነው። ስለ ሰላምና አንድነት የሚዘመርበት፣ ስለመጪው ጊዜ መልካም ምኞት የሚገለጥበት፣ ሁሉን ላደረገ ፈጣሪ ምስጋና የሚቸርበት የአብሮነት በዓል ነው። ኢሬቻ የሰው ልጅ ከተፈጥሮ ጋር ያለው ጥብቅ ቁርኝት የሚገለጽበት የገዳ ስርዓት አንዱ አካል ነው፡፡ የኢሬቻ እሴቶች ጠንካራ ህብረ-ብሔራዊ አንድነት ያላት ሀገር ለመገንባት የሚያግዙ ናቸው። አንድነት፣ ወንድማማችነት፣ አብሮነት፣ ሰላም፣ ፍቅር፣ ዕርቅ እና ሌሎችም ተጠቃሽ የመልካም እሴቶች መገለጫ ነው። በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ ሳይንስ እና ባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በማይዳሰስ ቅርስነት የተመዘገበው የገዳ ስርዓት አንዱ እሴት ኢሬቻ ሲሆን፤ ለሀገር ማንሠራራትና ሁለንተናዊ ብልጽግና መረጋገጥ መሠረት ይሆናል፡፡ ኢሬቻ አብሮነት የሚጸናበት፣ የወንድማማችነትና እህትማማችነት እሴት ይበልጥ የሚጎላበት፣ አሰባሳቢ ትርክት የሚጎለብትበት፣ ሁሉም በጋራ የሚያከብረው የፍቅር፣ የአንድነት እና የአብሮነት ማሰሪያ ከፍ ያለ በዓል ነው፡፡ ኢሬቻ በጋራ የሚያከብሩትና የዓለም ቱሪስቶች የሚታደሙበት ሲሆን፤ ሕብረ ብሔራዊ አንድነትና የኢትዮጵያ ድንቅ ባህል ጎልቶ የሚታይበት ነው፡፡ የዘንድሮውን የኢሬቻ በዓል አከባበር ሀገራዊ ማንሰራራት በተግባር የተረጋገጠበት ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ተመርቆ ዓለም የኢትዮጵያን መቻል በተግባር ባየበትና ሌሎች ለሀገር ማንሰራራት ዕውን መሆን መሠረት የሚጥሉ ትላልቅ ሀገራዊ ኘሮጀክቶች ይፋ በተደረጉበት ማግስት መሆኑ ለየት ያደርገዋል፡፡   በዓሉ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የመላው ኢትዮጵያዊያንን ሕብረት የሚንጸባረቅበት ሆኖ በተለያዩ አከባቢዎች በድምቀት እየተከበረም ይገኛል፡፡ በልመናው፣ በምርቃቱ፣ በምስጋናው ሁሉ ሀዬ! ሀዬ! ሀዬ! (አሜን! አሜን! አሜን!) የሚሉ ድምፆች ይስተጋባሉ። Hayyee! Hayyee! Hayyee! Hayyee! Hayyee! Hayyee! Waaqa Uumaa, Waaqa Uumamaa ፍጥረትን የፈጠርክ ፈጣሪ Gurraacha garaa garbaa የእውነትና የሰላም አምላክ! Dogoggora nu oolchi ከስህተትና ከክፉ ነገሮች ሁሉ ጠብቀን! Dacheef nagaa kenni ለምድራችን ሰላም ስጥ! Laggeenif nagaa kenni ለወንዞቻችን ሰላም ስጥ! Olota keenyaaf nagaa kenni ከጎረቤቶቻችን ጋር ሰላም ስጠን! . . . Loowan keenyaaf nagaa kenni " ለሰውም ለእንስሳቱም ሰላም ስጥ!" በማለት ይመረቃል። ሕዝቡም ይሁንልን ይደረግልን ሲል "አሜን! አሜን! አሜን!” ይላል። የዘንድሮው የኢሬቻ በዓል መስከረም 24 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሆራ ፊንፊኔ እንዲሁም በማግስቱ እሑድ መስከረም 25 ቀን በቢሾፍቱ ሆራ ሀርሰዲ " ኢሬቻ ለሀገር ማንሰራራት " በሚል መሪ ሐሳብ ይከበራል። የክራምት ወራት እንዳበቃ የሚከበረው "ኢሬቻ መልካ" Irreecha Birraa (በውኃ ዳርቻ የሚከበር) ሲሆን፤ በዓመቱ አጋማሽ ላይ "ኢሬቻ ቱሉ" Irreecha Arfaasaa ደግሞ በተራራማ ቦታ ይከበራል። ኢሬቻ መልካ የሚከበረው በመስከረም ወር ከመስቀል በዓል በኋላ ነው። የክረምት ወራት የዝናብ፣ የደመና፣ የጭቃና የረግረግ ወቅት አልፎ ለፈካው ወራት በመምጣቱ ምስጋና የሚቀርብበት ነው። ይህ ከማህበራዊ መስተጋብር አኳያም ሰዎች የሚሰባሰቡበትና የሚገናኙበት ነው። ከባዱ የክረምት ወቅት አልፎ ብርሃን (ብራ) ስለደረሰ ለዚያ ምልክት ይሆን ዘንድ የለመለመ እርጥብ ሣር ይዘው ወደ ወንዝ በመውረድ ንጹህ ውሃ ውስጥ እየነከሩና እየረጩ ለፈጣሪ ምስጋና የሚያቀርቡበት ነው፡፡ ኢሬቻ ቱሉ የሚከበረው የበጋው ወራት አልፎ የበልግ ዝናብ በሚጠበቅበት ወቅት ነው። በዚህም ፈጣሪ ''እርጥበት አትንፈገን፣ ወቅቶች ጊዜያቸውን ጠብቀው ይምጡ፤ የዝናብ ንፋስ ስጠን'' በማለት ለፈጣሪ ተማጽኖ የሚቀርብበት ነው። "ይህን ተራራ የፈጠርክ ፈጣሪ ወቅቱን የሰላም አድርግልን፣ የሰላም ዝናብ አዝንብልን፣ ጎርፍን ያዝልን፣ የተዘራው ፍሬ እንዲያፈራ እንለምንሃለን" እያለ በኢሬቻ ቱሉ ላይ ፈጣሪውን ይለምናል፡፡ በኢሬቻ በዓል የፈጣሪ ምህረት፣ ዕርቅ፣ አብሮነት እና በዓሉ የሰላም በዓል እንዲሆን ከላይ በተጠቀሰው መልኩ ኦሮሞ ፈጣሪውን ይጠይቃል፤ ይማፀናል፤ ለተደረገለትም ነገር ሁሉ ያመሰግናል። ኢሬቻ ምድርን እና ሰማይን ለፈጠረው "ዋቃ" "Waaqa" ምስጋናውን ለማድረስ የሚከበር ሲሆን፤ በዕድሜ ልዩነት ሳይገደብ ለዘመናት በጋራ፣ በአንድነትና በፍቅር ሲከበር ቆይቷል። በዝናባማው የክረምት ወቅት በጅረቶችና ወንዞች መሙላት ምክንያት ተራርቆ የቆየው ዘመድ አዝማድ በኢሬቻ በዓል ማክበሪያ ሥፍራ ይገናኛል፤ ይጠያየቃል፤ ናፍቆቱንም ይወጣል። አባቶች ክረምት በለሊት ይመሰላል ይላሉ። ለሊት ደግሞ ጨለማ ነው። ጨለማው ሲነጋ ደግሞ ብርሃን ነው፤ ብርሃን ደግሞ ውበት ነው፤ መታያና መድመቂያም ነው። ለዚህ ነው በኢሬቻ በዓል አከባበር ላይ ሁሉም ውብ የባህል ልብሱን በመልበስ በደስታ በዓሉን ለማክበር የሚመጣው። ሕዝቡ በዓሉ ወደ ሚከበርበት ሥፍራ የሚሄደው በተናጠል ሳይሆን በሕብረትና በአንድነት ነው፡፡ ለዚህ ነው ኢሬቻ የአንድነትና የአብሮነት በዓል ነው የሚባለው። ኢሬቻ የወንድማማችነትና የአንድነት አርማ ሲሆን፤ የብሩህ ዘመን ማብሰሪያ፣ የህብረ ብሔራዊ አብሮነት ማስተሳሰሪያም ጭምር ነው፡፡ በኢሬቻ ልዩነት የለም፤ ፀብ የለም፤ ክፋት የለም፤ ይልቁንም ምስጋና ይበዛል፤ ፍቅር ይሰፍናል፤ አብሮነት ያብባል፣ አንድነት ይጸናል። ኢሬቻ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው የሰላምና የአብሮነት ምልክት ነው። የኢሬቻ በዓልን ለማክበር የሚወጣው ታዳሚም እንደ እርጥብ ሣር ወይም አበባ ያለ እርጥብ ነገር በእጁ ይዞ የበዓሉን ስነ-ስርዓት ያከናውናል። ይህን የሚያደርገውም "ፈጣሪያችን ሆይ አንተ ያፀደቅከው ነው አብቦ ፍሬ ያፈራው፤ ለዚህም እናመሰግንሃለን" በማለት የፈጣሪን መልካምነት ለማሳየት ነው። በሌላ በኩል እርጥብ ሣር የልምላሜ ምልክት በመሆኑ የመልካም ምኞት መግለጫም ስለሆነም ነው በኢሬቻ በዓል እርጥብ ሣር የሚያዘው። የኢሬቻ በዓል ሲከበር ከሚከወኑ ሥርዓቶች መካከል ሴቶች ሲቄ፣ እርጥብ ሣር እንዲሁም ጮጮ ይዘው ከፊት ሲመሩ አባ ገዳዎች ደግሞ ቦኩ፣ አለንጌ እና ሌሎችንም በበዓሉ ሥርዓት የሚፈቀዱትን ሁሉ በመያዝ ወደ ሥርዓቱ አከባበር እንዲህ እያሉ ያመራሉ። ኦ ያ መሬሆ…………………መሬሆ መሬሆ………………… መሬሆ ያ ዋቃ ኡማ ሁንዳ መሬሆ………………… ያ መሬሆ መሬሆ………………… መሬሆ ያ ዋቃ ለፋ ኡምቴ መሬሆ………………… ያ መሬሆ መሬሆ………………… መሬሆ ያ ዋቃ መልካ ኡምቴ መሬሆ………………… ያ መሬሆ መሬሆ………………… መሬሆ እያሉ ያመራሉ። የሁሉ ፈጣሪ፣ ምድርን የፈጠርክ፣ ወንዙን የፈጠርክ . . . ምስጋና ለአንተ ይሁን በማለት ያመሰግናሉ፤ ይዘምራሉ። የኢሬቻ በዓል ሥነ-ሥርዓት በአባመልካ ተከፍቶ በአባ ገዳዎች ተመርቆ ከተጀመረ በኋላ መላው ሕዝብ በአንድነት ሥርዓቱን ያከናውናል። ኢሬቻ ሁሉም በጋራ የሚያከብረው፣ የሁሉም ማጌጫ፣ መድመቂያ እና የአብሮነት መገለጫ ነው። የበዓሉ ታዳሚዎች ከዋዜማው ጀምሮ በሆረ ፊንፊኔና በሆረ ሀርሰዲ በመሰባሰብ፤ የተለያዩ ባህላዊ ጭፈራዎችን በማዜምና ምስጋና በማቅረብ አድረው በነጋታው ዋናውን የምስጋና በዓልም ያከናውናሉ፡፡ የበዓሉ ታዳሚዎች የደስታና የምስጋና ምልክት የሆነውን ባህላዊ ነጫጭ ልብስ ለብሰው፣ ባህልን የሚያንፀባርቁ የተለያዩ ሁነቶችን በመከወን ልዩ ልዩ ዜማዎችን በማዜም፣ ግጥሞችን በማቅረብ፣ ወደ ፈጣሪ በመጸለይ እና ምስጋና በማቅረብ ሥርዓቱን ያከናውናሉ፡፡ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች የሚታወቁበትን ባህላዊ ልብስ በመልበስ በቋንቋቸው ፈጣሪን እያመሰገኑ በዓሉን በአንድነት ያከብራሉ። ከሃገር ውስጥና ከውጭ ሀገር በርካታ ታዳሚዎች የሚሳተፉበት የኢሬቻ በዓል የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦችን ከማቀራረብና ህብረ ብሔራዊ አንድነትን ከመገንባት ረገድ ትልቅ አስተዋጾኦ ያለው ነው፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ-ኢትዮጵያውያን የሆራ ፊንፊኔ እና የሆራ ሀርሰዲ በዓላት ላይ ለመታደም ወደ አገር ቤት ይመጣሉ። የውጭ አገራት ጎብኚዎችና እንግዶችም በትዕይንቱ ይታደማሉ። ለአብነትም ባሳለፍነው ዓመት ከኬንያ፣ ሩዋንዳ እና ታንዛኒያ አገር የመጡ ልዑካን በበዓሉ ላይ በመታደም የበዓሉን ትልቅነት እና የኢትዮጵያውያን የአብሮነት መገለጫ መሆኑን መመስከራቸው ይታወሳል። አያሌ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳዎች ያሉት ይህ የምስጋና በዓል እውነተኛ ወንድማማችነት የሚታይበት፣ አንድነት የሚጎላበት፣ አብሮነት የሚጠናከርበት፣ ሰላምና ተስፋ የሚታወጅበት አገራዊ እሴት ነው። በባህል አልባሳትና ጌጣጌጦች፣ ባህላዊ ምግቦችና ሌሎች ዘርፎች ላይ የተሰማሩ ግለሰቦችና ተቋማት ኢሬቻና መሰል የአደባባይ በዓላትን እንደመልካም የገበያ አማራጭ ይጠቀሙባቸዋል። የኢሬቻ በዓል ለቱሪዝም ፍሰት የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ጉልህ ነው፤ በርካታ የባህር ማዶ እና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎች የሚታደሙበት በዓል ነው፡፡ በዓሉ ትልቅ የቱሪዝም መስህብ ሲሆን፤ ዘርፉን በማጠናከር እና ብሔራዊ ልማትን በማሳደግ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ከፍ በማድረግ ረገድ ትልቅ ሚናንም የሚጫወት ነው፡፡ ኢሬቻ ባህላዊ አልባሳትና ቁሳቁሶች በስፋት የሚተዋወቁበት ታላቅ መድረክ ነው። በእርግጥም ይህንን ውብ የጋራ እሴት ጠብቆ ለትውልድ ማስተላለፍ ያስፈልጋል። ኢሬቻ የምስጋና በዓል ነውና በምስጋና እንደጀመርን በምስጋናና ምርቃት እንሰነባበት። "ሀዬ! ሀዬ! ሀዬ! ከመጥፎ ነገር ጠብቀን! ንጹህ ዝናብ አዝንብልን! ከእርግማን ሁሉ አርቀን! እውነትን ትቶ ከሚዋሽ አርቀን! ከረሃብ ሰውረን! ከበሽታ ሰውረን! ከጦርነት ሰውረን! ሀዬ! ሀዬ! ሀዬ!        
በትግራይ ክልል የመስቀል በዓል አከባበር
Sep 27, 2025 1127
የመስቀል በዓል በሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች በልዩ ድምቀት ከሚከበሩ በዓላት መካከል አንዱ ነው። በዓሉ እንደየአካባቢው ባህላዊና ሃይማኖታዊ ትውፊቱን ጠብቆ በተለያዩ ሁነቶች ይከበራል። በትግራይ ክልልም የመስቀል በዓል እንደሌሎች የኢትዮጵያ አካባቢዎች ሁሉ በናፍቆት ከሚጠበቁና በድምቀት ከሚከበሩ በዓላት ተርታ ይመደባል። ለዚህም ሲባል የተለያዩ ዝግጅቶች ከበዓሉ ዋዜማ በፊት እንዲጠናቀቁ የሚደረግ ሲሆን፥ በተለይ በየዓመቱ መስከረም 16 እና 17 ዘመድ አዝማድ ተጠራርተው የሚገናኙበት የፍቅርና የአብሮነት በዓል ሆኖ ይከበራል። የክርስቶስ ግማደ መስቀል በንግስት ኢሌኒ አማካኝነት መገኘቱን በማሰብ በየዓመቱ መስከረም አጋማሽ ላይ የሚከበረው የመስቀል በዓል የመስቀል ኃያልነት፣ እውነት በተደበቀበት ለዘላለም እንደማይቀርና ፍቅርን አብዝቶ የሚሰበክበት ከዚህ ባለፈም እርቅ የሚወርድበትና ደስታ የሚገለጽበት አጋጣሚ መሆኑም ይገለጻል። በትግራይ የበዓሉን ታላቅነትና ክብር ለማድመቅ ምእመናን ጽዱ ልብስ ለብሰውና የተለያዩ ዝማሬዎችን በማሰማት ደመራ ወደሚደመርበት ሥፍራ ችቦ ይዘው በመሄድ ደምራውን በማቀጣጠል የሚያከበሩት ሲሆን፣ በእለቱ የቤት እንስሳት ጭምር ቀንዳቸውና ጀርባቸው ላይ ቅቤ ተቀብተው እንዲያርፉ ይደረጋል። ዘመድ አዝማድ፣ ጎረቤታሞች፣ አብሮ አደጎችና የበዓሉ ታዳሚ እንግዶችም ተሰባስበው ማለዳ ላይ ገንፎ በማዘጋጀት ይመገባሉ። የእንስሳት እርድ በማከናወን ባህላዊ መጠጦችን በማዘጋጀት በዓሉን የፍቅር፣ የመሰባሰብ፣ የአንድነትና ተካፍሎ የመብላት በዓል መሆኑን በተግባር የሚያሳይበት ክስተት ሆኖ ያልፋል። "ዓኾይ ዓኾኾይ" የጎመን ምንቸት ውጣ የገንፎ ምንቸት ግባ በማለትም ችቦ ተሎኮሶ በየቤቱ በመዞር የምረቃ እና ለሚቀጥለው ዓመትም በሰላምና ደስታ እንዲሁም እድሜና ጤናን በመመኘት ይከወናል። የአደባባይ በዓል የሆነው የመስቀል በዓል በዝማሬ፣ በሆታና እልልታ የሚገለጽ ሲሆን፤ ወርሃ መስከረም እሸት አሽቶ አበቦች አብበውና ምድር ልዩ ልምላሜን ተላብሶ የሚታይ በመሆኑ ልክ በታሪኩ እንደሰፈረው የሰላም፣ የእውነትና የአንድነት በዓል መሆኑን በተግባር የሚታይበት ነው።
የሀመሯ እናት- የደስታ እንባ
Sep 11, 2025 1532
የሀመሯ እናት- የደስታ እንባ በጣፋጩ ሰለሞን (ከጂንካ) በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገኘው ሐመር ወረዳ የሐመር ብሔረሰብ ዘመን በተሻገሩ ባህላዊ ሥርዓቶች ይታወቃል። በዚህ አካባቢ ከሚዘወተሩትና በብዛት ከሚታወቁት ባህላዊ ሥርዓቶች መካከል “ኢቫንጋዲ እና ኡኩሊ” የተባሉ ባህላዊ ጨዋታዎች ይጠቀሳሉ። “ኡኩሊ”በሐመሮች ዘንድ በስፋት የሚታወቅ ባህላዊ ጨዋታ ሲሆን ለአቅመ አዳም የደረሰና ከብት ለመዝለል ዝግጁ የሆነ የሐመር ወጣት የሚጠራበት የማዕረግ ስም ነው፡፡ “ኡኩሊ” ከብት በሚዘለልበት ዕለት ሥርዓቱ በሚፈጸምበት ሥፍራ ላይ በቅርብም ይሁን በሩቅ ያሉ የወጣቱ ዘመዶች ተጠርተው የሚከናወን ባህላዊ ሥርዓት መሆኑ ይታወቃል። “ኢቫንጋዲ” ደግሞ በሐመሮች ዘንድ በስፋት የሚታወቅ ባህላዊ ጭፈራ ሲሆን ትርጉሙም “ኢቫን” ማለት “ ማታ” ሲሆን “ጋዲ” ማለት ደግሞ “ጭፈራ” ማለት መሆኑ ይነገራል። ኢቫንጋዲ በአዝመራና በደስታ ወቅት በሥራ የደከመን አእምሮና አካል ለማዝናናት ሲባል የሚከናወንና የሀመር ወጣቶች በጉጉት የሚጠብቁት ባህላዊ ጭፈራ ነው። በዚህ ባህላዊ ጨዋታ ላይ የሐመር ወጣት ወንዶችና ልጃገረዶች አምረውና ተውበው በጨረቃ ብርሃን ይጨፍራሉ። የኢቫንጋዲ ጭፈራ በሶስት ቀን አንድ ጊዜ በሐመር መንደሮች በምሽት ከጨረቃ ድምቀት ጋር አብሮ ይደምቃል። “በጨረቃ ብርሃን አየኋት በማታ ኢቫንጋዲው ቦታ” የተባለላቸው የሃመር ውብ ልጃገረዶችም ከጨረቃ ብርሃን ጋር ደምቀው የሚታዩበት ዕለት ይሆናል። በወጣትነታቸው በዚሁ ባህላዊ ሥርዓት ያለፉት የሀመሯ እናት- ወይዘሮ ባሎ ኡርጎ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ እናት ናቸው። በሐመር ወረዳ ዲመካ ከተማ የሚኖሩት ወይዘሮ ባሎ፤ በደሳሳ ጎጇቸው ሲያገኙ በልተው ሲያጡ ደግሞ ኩርምት ብለው ያሳለፉባቸው ጊዜያት እንዳሉ ያስታውሳሉ። በደሳሳ ጎጆ እየኖሩ ዝናብ ሲመጣ የጎርፍ፣ ብርድና ዶፉ ስጋት ላይ ጥሏቸው እንደኖሩ ያነሳሉ፤ በበጋ ወራት ደግሞ የሚነፍሰው ነፋስና ሀሩሩ ጸሃይ ይፈትናቸው እንደነበር ይናገራሉ። ከእለታት አንድ ቀን ወጣቶችና ጎልማሶች ጭምር ሰብሰብ ብለው መጥተው “ቤትዎን በነፃ ልናድስልዎት ነው ሲሉኝ አላመንኳቸውም ይላሉ። የእውነታችሁን ነው አልኳቸው? አዎን ቤትዎን አፍርሰን ልንሰራልዎት ነው” ብለው አረጋገጡልኝ በማለት ሁኔታውን በደስታ እንባ ታጅበው ያስታውሳሉ። በተባለው መሰረትም በክረምቱ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የቤታቸው እድሳት ተጀምሯል። የኢዜአ ሪፖርተር በስፍራው ተገኝቶ ወይዘሮ ባሎን ባነጋገራቸው ወቅት “ሰው በሚያስፈልገኝ ጊዜ ሰዎች ሁነው የተገኙ ወገኖቼ ችግሬን ለመፍታት በአካል ተገኝተዋል፤ በጣም ደስ ብሎኛል፤ የመኖርን ተስፋ እንድሰንቅ አድርገውኛል በማለት ደስታቸውን በእንባቸው ጭምር ታጅበው ገልጸዋል። የሀመሯ እናት ቤታቸው በፍጥነት ታድሶ የሚረከቡ፣ በቀጣይም አስፈላጊው እገዛና ድጋፍ የሚደረግላቸው መሆኑን የቤቱን እድሳት ያስጀመሩት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር አረጋግጠዋል። እንደ ወይዘሮ ባሎ፤ ያሉ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖችን የማገዝና የመደገፍ ሃላፊነት አለብን ያሉት ሃላፊው፤ የመረዳዳትና የመተጋገዝ ባህል ጎልቶ እንዲቀጥል ሁላችንም የድርሻችንን ልንወጣ ይገባል ብለዋል። የቢሮው የማኔጅመንት አባላትና ሰራተኞች ለወገኖቻቸውያላቸውን አለኝታነት በተግባር በማሳየታቸውም አመስግነዋል። የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ፤ የዘንድሮ የክረምት በጎ ፈቃድ ተቋማት፣ግለሰቦች፣ወጣቶችና አዛውንቶች ሳይቀር የተሳተፉበት እና የበርካቶችን ችግር መፍታት የተቻለበት መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ማኔጅመንት አባላትና ሰራተኞች የወይዘሮ ባሎን ቤት ለማደስ በመምጣታቸው አመስግነው፤ ለሌሎች ተቋማትም አርአያ የሚሆን የመልካምነት ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ በተያዘው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ቤቶችን ጨምሮ የዞኑን ማህበረሰብ ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም በዞኑ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ወገኖችን የመደገፍና ሰው ተኮር የልማት ስራዎችን በስፋት የማከናወን ተግባር በተጠናከረ መለኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል።
የአባይ የቁጭትና የወቀሳ ጊዜ አበቃ!  
Sep 9, 2025 1181
የአባይ የቁጭትና የወቀሳ ጊዜ አበቃ! (በቀደሰ ተክሌ - ከሚዛን አማን) አኩርፎ ከቤት ቢወጣ ለመመለስ ሸምጋይ አጥቶ በሰው ሀገር ተንከራታች ልጓም አልባ ሆኖ የኖረው አባይ ከኢትዮጵያ አፈር፣ ማእድናትና ሌሎችንም ሃብቶች ጠርጎ በመውሰድ ለዘመናት ሲፈስ ኖሯል። ከኢትዮጵያ እምብርት በመነሳት አገራትን አቆራርጦ የሚያልፈው፣ የዓለማችን ታላቁ ወንዝ አባይ በጋና ክረምት ሳይል በመፍሰስ የብዙዎች የህይወት ምንጭ ሆኖ አሁንም ፍሰቱን ቀጥሏል። የኢትዮጵያ ልጅ የኢትዮጵያውያን አብሮነት ምሰሦ - የወንዞች ንጉሥ ታላቁ አባይ! አሁን ልጓም ተበጅቶለት በፍትሃዊነት ሁሉንም ለመጥቀም ተዘጋጅቶ የማይነጥፈው ጅረት ዘላለማዊ የመፍሰስ ሂደቱ እንደቀጠለ ነው። ኢትዮጵያውያን አመሉ ለከፋ፤ እሺ በጀ አልል ብሎ በእንቢታ ልቡን ባጸና ልጅ አብዝተው ያዝናሉ። የሀዘናቸው ጥግም በሕይወት ሳለ የሞተ ያክል በእንጉርጉሮ ሙሾ ያወርዱለታል። አባይም ይህ እጣ ፈንታ ገጥሞት "አመፀኛ ውሃ" ተብሎ በወቀሳ ተዚሞለታል። ለኢትዮጵያ ለዘመናት ሳይታዘዝ የኖረው አባይ የአዛዥ እጦት እንጂ በእምቢታ አልነበረም። በዚህ ውጣ በዚህ ግባ ባይ አጥቶ ቦዘነ። በዚህም ተራራውን እየሸሸ ቁልቁል እየተምዘገዘገ፣ ሲሻ እየጬሰ ቁልቁል ወርዶ ከዐለት ጋር እየተጋጨ መዳረሻውንና ማደሪያውን ይናፍቃል። በዚህም ቤቱን ረሳ። ወላጆቹን ትቶ ባእዳንን ብቻ ጦረ፣ ፊቱን በፍጹም ወደ ኋላ እንዳይመልስ እንደ ሎጥና ቤተሰቦቹ ተገዘተ። አባይ የባእዳንን ግዝት ከተፈጥሮ ጋር አስተባብሮ በመጠበቅ ሀገሩን ለቆ ከመውጣት ውጭ ቢደክመው የማረፍ፥ ቢመቸው የማልማት መብት ሊያገኝ አልቻለም። ይህ በኢትዮጵያ ልብ ውስጥ ቁጭት ፈጥሮ ከትውልድ ወደ ትውልድ ተሸጋገረ። ኢትዮጵያ ለታላቅ ልጇ ማረፊያ ሠርታ ጎጆ ልታወጣ ቋመጠች። ፈተናው በዛ የፖለቲካ መልክ ይዞም አቅሟን ተፈታተነ። ስደተኛው አባይን ስላሳረፉት እርሱም ስለመገባቸው የግል ሀብት አድርገው የቆጠሩት የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ጫና ፈጥረው የሀሳብ ጽንሱን ከታሪካዊና ቀጣናዊ ጠላቶች ጋር እየተባበሩ አቋረጡት። አባይን ገድቦ የመጠቀም የዘመናቱ የኢትዮጵያ መሪዎች ጉጉቱ ህልም ሆኖ ሐዘኑ ከነ ቁጭቱ ቀጠለ። እንጉርጉሮ ወቀሳ በበዛባቸው ስንኞች ቋጥሮ መዜሙን ቀጠለ። የኢትዮጵያ ዐይኖች ጀግንነት በአባይ ሲሸበብ ማየት አንገሸገሻቸው። የበይ ተመልካች መሆንና ከጓሯቸው ሞፈር አስቆርጦ መራብ አመማቸው። ኢትዮጵያዊነት ከዘመን ዘመን የማይነጥፍ፥ ልብ ለልብ የተሳሰረ ትውልድ ማንነት ማሳያ ሐውልት ነው። ትላንት ዛሬን እያቃና ነገን የሚገነባበት ሀገራዊ ራእይ ያላቸው መሪዎች ትስስር በአባይ ሲንጸባረቅ ይስተዋላል። ከ1929 እስከ 1950ቹ ያለው የአባይ ፖለቲካ ጉዳይ በብዙ ድርድሮችና ስምምነቶች ታጀበ። የጫና ፈተናው አየለና ገንብቶ የመጠቀም ጥንስስን ለቀጣይ ትውልድ እንዲሸጋገር አደረገ። ያኔ ነገን የተመለከተ ዐይን "ልጆቻችን ይሠሩታል" የሚል ቃል ሰጠና ኢትዮጵያ ልጆቿን በተስፋ ተጠባበቀች። ዘመን አለፈ ትውልድ ተተካ ልጆችም ተወለዱና የተስፋ ቀጠሮ ደረሰ ወርሃ መጋቢት 2003 ዓ/ም። በዚህ ቀን የታላቁ ኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ዜና በቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ተበሰረ። ኢትዮጵያ እልል አለች፤ "እንጉርጉሮ ይብቃ" ተባለ በዜማ በዝማሬ አባይ ተሞገሰ። የአባይ የወቀሳ ጊዜ ተጠናቀቀ- የቁጭት ጊዜ አብቅቶ የስኬትና ማንሰራራት ጊዜ መጣ። ለግድቡ የ14 ዓመታት የግንባታ ሂደት ከአንድ ብር ጀምሮ አስተዋጽኦ ያደረጉ፣ በእውቀትና በጉልበት የተጉ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ የደስታ ቀንም እውን ሆነ። በጉባ ሰማይ ስር አዲስ ክስተት፣ አዲስ ምዕራፍ፣ አዲስ ስም ተተከለ። አባይ ከሚል ነጠላ ስም ወደ "ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ" ተሻገረ። የድግቡ ሃይቅም "ንጋት" የሚል መጠሪያ ወጥቶለት ለኢትዮጵያ የንጋት ጸሃይ እየወጣች መሆኑን ለሁላችንም ብስራት ሆነ። "እንኳንም ጀመርን፣ እንኳንም በር ተከተፈተልን" እንጂ ያሉት ልበ ኩሩና ክንደ ብርቱ ኢትዮጵያውያን ጫናዎችን በአይበገሬነት መንፈስ ድባቅ እየመቱ ጉዞ ወደ ፊት ቀጠሉ። ወደ ተግባር ገብተው "ሕይወታችንንም ቢሆን ለአባይ አንሰስትም" አሉ። ግድቡን እንሠራለን ብለው የጀመሩት ኢትዮጵያውያን ናቸው። ከነ አባባላቸው "የነብር ጭራን አይያዙ፥ ከያዙም አይለቁ" ነውና ሥራውን ስለጀመሩት የአባይ ግድብ ጉዳይ ቀዳሚ አጀንዳቸውና ደም ስራቸው ሆኖ ቀጠለ። እንደ ዐይን ብሌናቸው ያዩ፣ ይጠብቁት እና ይሳሱለት ጀመር። የአልሸነፍ ባይነት ወኔን ከጀግንነት ጋር አጣምረው የያዙ ኢትዮጵያውያን የጠላት ነቀፋና ፕሮጀክቱን የማኮላሸት ሴራን እንደ ድር አብረው ተከላከሉ። የ"እንችላለን" ትርክትን በተግባር ነፍስ እየዘሩ እጅ ለእጅ ተያይዘው ጉዟቸውን ከሕዳሴ ጋር ቀጠሉ። በጉባ ምድር ላይ የአንድነታቸውን ቋሚ ሐውልትም ተከሉ። ኢትዮጵያውን ከአድዋ ጦርነት ወዲህ የአንድ ቃል ተናጋሪ የአንድ ልብ መካሪ ሆነው የተከሰቱበትና በአንድ የተመሙበት ትልቁ የታሪክ አሻራ አባይ በሕዳሴ ሆነ። የተማሪ ቦርሳ፣ የእናቶች መቀነት፣ የአረጋውያን የጡረታ ደብተር፣ የአርሶ አደሮች ጎተራ፣ የአርብቶ አደሮች በረት፣ የመንግሥት ሠራተኛው ፔሮል፣ የነጋዴው ኪስ እና የዳያስፖራ ዋሌት ሳይቀር በአባይ ላይ አሻራ አለው። የሕዳሴው ግድብ ውዝግብ ኢትዮጵያ ራሷን በዓለም መድረክ ከፍ አድርጋ ያሳየችበት ትልቅ አጋጣሚ ነው። ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የደረሰውን ውሃ አይሞላ ክስ በብስለት መክታ እውነትን ለዓለም ሕዝብ አስገንዝባለች። በዚህም የዓለም አቀፍ ሕግ አዋቂነቷንና አክባሪነቷን፣ የጋራ ተጠቃሚነት ፍላጎቷንና ለሰላም ያላትን አቋም ቁልጭ አድርጋ አረጋግጣለች። ድርድሮችን በድል የሚቋጩ ልጆቿ ደግሞ ኢትዮጵያውያን በሁሉም ዘርፍ ብቁ የመሆናቸው ነጸብራቅ ሆነው ተከሰቱ። ዘርፈ ብዙ የዲፕሎማሲ ሥራው ከማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚ እስከ ጉምቱ አምባሳደሮች በተናበበ መልኩ ብቅ ብሎ አጀብ አስብሏል። ድርድሩ በመስመሩ፣ የዲፕሎማሲ ሥራው በሜዳው ፖለቲካ እና ሌላው የሀገር ጉዳይ በየፈርጁ እየቀጠለ የሕዳሴው ግድብም ለደቂቃ እንኳ ሳይቆም ይሠራ ነበር። ይህ የመብቃት፣ የማደግ፣ በጥበብ የመበልጸግ፣ በሀሳብና አቅም የመብሰል ሀገራዊ ማሳያ ነው። ለብዙ የአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ የሚሆን አሻጋሪ የተግባር ልምምድ መሆኑም አያሻማም። ለዚህ ግድብ ስኬት ደግሞ የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን መሪ ሆነው ብቅ ያሉትን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶር) ማንሳት ግድ ይላል። አዛዥ አጥቶ ቦዝኖ የነበረውን ጊዜ ለመካስ ና ብሎ የሚጣራውን አዛዥ "አቤት" ብሎ ትዕዛዝ ለመቀበል አባይ አላቅማማም። አሁን በሙሉ ልቡ ወደ ጫጉላ ቤቱ ገብቷል። የመስከረሙ ሙሽራ የቤት ሀብት ዘርፎ ለባዕድ አሳልፎ ከመስጠት ተቆጠበ። የበረሃው ሀሩር ሳይመታው በሀገሩ እፎይ ብሎ ብርሃንም ምግብም፣ ሀብትም ክብርም መሆን ጀመረና የኢትዮጵያን ክብር ዳግም ከፍ አደረገ። ሰው ተፈጥሮን ሲያዝ እሺ ይላል፥ ዝም ካሉት በራሱ ፍላጎት ይሔዳል። ይህ ተፈጥሯዊ የአባይ ግብር ተቀይሮ በሰዎች መታዘዝ ጀመረ። አፈርና ውሃ ማስቀረት ብቻ ሳይሆን ግዙፍ የብርሃን ምንጭ ሆኖ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ብርሃን መሆን ጀምሯል። በሕዳሴ ግድብ ታዞ ፊቱን ወደ ልማት ሥራ ያዞረው አባይ ያለፈውን ለመካስ ብዙ ጸጋዎችን ይዞ ተከሰቷል። የዓሳ ምርት፣ ግዙፍ ሀይቅ ከደሴቶች ጋር አንጣሎ በመያዝ የኢኮ ቱሪዝም ዘርፍ መሪ ሊሆን ቆርጦ ተነስቷል። አብሮ የመልማት የኢትዮጵያ ጽኑ ፍላጎት በወለደው እሳቤ ህዳሴ ግድብ የጎረቤት አገራት ሃብት ጭምር በመሆን ለማገልገል ተዘጋጅቷል። አባይ ሆይ ስምህ ከወቀሳ ወጥቶ በሙገሳ ስለተተካ እንኳን ደስ አለህ! እናቴ ሆይ የተፈታው መቀነትሽ ሀይል ስላመነጨ ለልጆችሽ ሀብት አውርሰሻልና ደስ ይበልሽ። ሀገሬ የብርሃን ዘመን ስለፈነጠቀብሽ እንኳን ደስ አለሽ! ሰላምና ፍቅር ለሁላችን ይሁን።
 የትውልዱ ድል፤ የብርሃን ጅረት
Sep 8, 2025 791
አቶ ዲሮ ቱፋና ዓለሚ በዳዳ በምዕራብ ሸዋ ዞን ወልምራ ወረዳ ነዋሪ ናቸው። አካባቢያቸው ለአዲስ አበባ ከተማ ቅርብ ቢሆንም እስካሁን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ማግኘት አለመቻላቸውን ያነሳሉ።   የኤሌክትሪክ ሃይል ሽፋን ባለመዳረሱ ምክንያት ኑሯቸው አስቸጋሪ ሆኖባቸዋል፤ ማገዶ መጠቀማቸው ደግሞ ለጤናቸው ተግዳሮት እየሆነባቸው መጥቷል። እነርሱ እንደሚሉት የማገዶ እንጨት ለማምጣት ረጅም ርቀት በመጓዝ ለእንግልት ተዳርገዋል። የቤንች ሸኮ ዞን ነዋሪዋ አበበች ደጎሽም በአካባቢያቸው የኤሌክትሪክ ሃይል ባለመኖሩ ምክንያት ሕይወታቸውን ፈታኝ አድርጎታል።   ልጃቸው ለማጥናት የሻማና ኩራዝ መብራት ለመጠቀም ትገደዳለች።   በዚህ ላይ ምግብ ለማብሰል ከሰል መጠቀማቸው በጤናቸው ላይ ችግር እየፈጠረ መጥቷል፤ በተለይ በመተንፈሻ አካላቸው ላይ ያጋጠማቸው እክል ለሀሳብ ዳርጓቸዋል። በምዕራብ ሸዋ ዞንና በቤንች ሸኮ ዞን ያሉት ሁለቱን ቤተሰቦች ተስፋ ያስተሳስራቸዋል። ለኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎታቸው ምላሽ ለማግኘት ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሚመነጨውን ሃይል በተስፋ ይጠባበቃሉ። በመላው ኢትዮጵያውያን ቁርጠኝነት፣ የገንዘብ መዋጮና የተቀናጀ ትብብር እውን የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ይዞ እየመጣ ካለው የ5 ሺ 150 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል ተቋዳሽ እንደሚሆኑ ይተማመናሉ። መጋቢት 24 ቀን 2003 ዓ.ም በቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መሠረተ ድንጋይ በቤንሻንጉል ጉምዝ ጉባ ወረዳ ከተቀመጠ ከዓመታት በኋላ መጠናቀቁን ተከትሎ እንደ አቶ ዲሮ ቱፋና ዓለሚ በዳዳ ያሉ ተስፋቸው ለምልሟል። ከሚያመነጨው የኤሌክትሪክ ሃይል ተቋድሰው መብራት በማግኘት ኑሯቸውን የሚያሻሻሉበትን መንገድ በተስፋ ይጠባበቃሉ። ለዚህም ነው ባለፉት ዓመታት ኢትዮጵያዊያን በዓባይ ወንዝ ላይ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ገንዘባቸውን፣ እውቀታቸውንና ጉልበታቸውን በማዋጣት የግድቡን ግንባታ በቁርጠኝነት ያካሄዱት። መነሻውን ከኢትዮጵያ አድርጎ 6 ሺ 696 ኪሎ ሜትር ርዝመት የሚጓዘው የዓባይ ወንዝ ከዓለማችን ረጃጅም ወንዞች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት ተጠቃሽ ነው። ረጅም ኪሎ ሜትር ለሚጓዘው የዓባይ ወንዝ 86 በመቶ የውሃ ድርሻ የምትሸፍነው ደግሞ ኢትዮጵያ ናት። ኢትዮጵያ የገነባችው ታላቁ የህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ለአቶ ዲሮና መሰሎቻቸው ኑሯቸውን ለማቃለል የሚያስችል የመብራት ሃይል ከማቅረብ ባሻገር ለጎረቤት አገራት የኤሌክትሪክ ሃይል በመሸጥ ትስስር ለመፍጠር የሚያስችል አቅም እንደሚሆን ነው ባለሙያዎች የሚገልጹት። ይህ ደግሞ የተፋሰሱ አገሮች በኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት መተሳሰር የሚያስችል፣ በጋራ በመልማት ዕድገታቸውን ለማፋጠን እድል የሚከፍት መሆኑን ነው ባለሙያዎች የሚስማሙት። ይህ ግን በቀላሉ የተገኘ ዕድል ላለመሆኑ ያለፉት ዓመታት ተግዳሮቶች ተጠቃሽ መሆናቸው አጽንኦት የሚሰጠው ጉዳይ ነው። የቀድሞው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የተደራዳሪ ቡድን አባልና የውሃ ሃብት አስተዳደር፣ ወሰን ተሻጋሪ ወንዞችና የሃይድሮ ዲፕሎማሲ አማካሪ ፈቅ አሕመድ ነጋሽ፤ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እንዲጓተት፣ መንግስትና ህዝብ ተስፋ ቆርጠው እንዲተውት ብዙ ሙከራዎች ቢደረጉም በኢትዮጵያውያን የጋራ ጥረት ማጠናቀቅ መቻሉን ያነሳሉ።   የዓለም አቀፍ የውኃ ሕግ ባለሙያው ከበደ ገርባ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያን ከዓባይ ውሃ ለመነጠል ዘርፈ ብዙ አደናቃፊ የዲፕሎማሲ ስራዎች ቢሰሩም ግንባታውን ማስተጓጎል ያለመቻሉን ነው አጽንኦት የሰጡት።     የቀድሞው የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትርና በአሜሪካ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ስለሺ በቀለ (ዶ/ር) በአንድ ወቅት ግንባታው እንዳይጠናቀቅ ከውጭ ሃይሎች ባለፈ በአገር ውስጥ የተለያዩ ተግዳሮቶች ገጥመውት እንደነበር መግለጻቸውን እዚህ ላይ መጥቀስ ይቻላል። በኢትዮጵያ ለውጥ ከመጣ በኋላ መንግስት ግድቡ ላይ ከፍተኛ ርብርብ በማድረግ በተሻለ ፍጥነትና ጥራት ተገንብቶ እንዲያልቅና ለታለመለት ዓላማ እንዲውል መስራቱ ተገልጿል። ኢትዮጵያ የተፋሰሱ አገሮች የዓባይ ወንዝን በፍትሃዊነት የመጠቀም አስፈላጊነትን የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ በመጀመር በተግባር የተገለጠ እርምጃ መውሰዷ በአካባቢው አገሮች ላይ ተስፋን አጭሯል። ለዚህም ነው የናይል ተፋሰስ አገራት በዓባይ ውሃ አጠቃቀም ላይ ፍትሃዊና ምክንያታዊ አጠቃቀም እሳቤ እንዲኖራቸው የናይል ተፋሰስ አገራት የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ሰነድ (CFA) እ.አ.አ በ2010 ተዘጋጅቶ አገሮች እንዲስማሙ እድል የተሰጠው። ይህም ለዓባይ ውሃ ምንም ድርሻ የሌላቸው የታችኞቹ ተፋሰስ አገራት እ.አ.አ በ1929 እና በ1959 የዓባይን ውሃ በብቸኝነት ለመጠቀም የተፈረሙትን የቅኝ ግዛት ውሎች ውድቅ የሚያደርግና በተፋሰሱ አገራት መካከል አዲስ የትብብር ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑን የዘርፉ ምሁራን ይገልጻሉ። የናይል ተፋሰስ አገራት የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ሰነድ እ.አ.አ በ2010 ለፊርማ ክፍት ከሆነ በኋላ ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ታንዛንያና ዩጋንዳ፣ ደቡብ ሱዳንና ብሩንዲ ፈርመዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የውሃ ሃብት መምህርና ተመራማሪ ኤርሚያስ ተፈሪ (ዶ/ር) እንደሚሉት፤ የማዕቀፍ ስምምነቱን ስድስቱ አገራት ሰነዱን በፓርላማቸው ካጸደቁ የናይል ኮሚሽን ማቋቋም ይችላሉ። እንደ ቀድሞው የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የተደራዳሪ ቡድን አባልና የውሃ ሃብት አስተዳደር ፣ወሰን ተሻጋሪ ወንዞችና የሃይድሮ ዲፕሎማሲ አማካሪው ፈቅ አሕመድ ነጋሽ፤ በአሁን ወቅት ስድስቱ አገራት ስምምነቱን መፈረማቸውን ተከትሎ የናይል ተፋሰስ ኮሚሽን ተቋቁሟል። የውሃ ሃብት መምህርና ተመራማሪ ኤርሚያስ ተፈሪ (ዶ/ር) እንደሚሉት፤ ከዓባይ ተፋሰስ አገራት መካከል ግብጽና ሱዳን የኤሌክትሪክ ሃይል ሽፋናቸው ከፍተኛ በመሆኑ ከኢትዮጵያ ጋር ሊነጻጸር የማይችል መሆኑን ነው የሚያነሱት። ይህም በጤና፣ በትምህርት እና በኑሮ ዘይቤ ላይ የሚያስከትለው አሉታዊ ተጽዕኖ ከፍተኛ ነው ይላሉ። ይህን ችግር ለማቃለልና ብርሃንን ለሁሉም ለማዳረስ ታላላቅ ፕሮጀክቶች ግድ ይላሉ ብለዋል። ኢትዮጵያውያን በ''እንችላለን'' መንፈስ ከተማሪ እስከ ሰራተኛ፣ ከጡረተኛ እስከ ወታደር፣ ከቤት እመቤት እስከ ባለሃብት ሁሉም በደረጃውና በአቅሙ በገንዘብ በሀሳብና በጉልበት ለመሳተፍ ቁርጠኛ አቋም በመያዝ የግድቡን ግንባታ እውን ለማድረግ ተረባርበዋል። የታላቁ ህዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤት ዋና ስራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር)፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን በራስ አቅም በራስ ዕውቀትና ሀብት የማይቻል የሚመስለውን ችለው ያሳዩበት አኩሪ ታሪክ ነው ይላሉ።   እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ መጻዒ ዕድሉን የተሻለ ለማድረግ ከዕውቀቱ፣ ከገንዘቡና ከጉልበቱ አዋጥቶ እውን ያደረገው የዳግማዊ ዓድዋ ድል መሆኑን የሚናገሩት ደግሞ የጥንታዊ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ፕሬዚዳንት ልጅ ዳንኤል ጆቴ ናቸው። የዓለም አቀፍ የውኃ ሕግ ባለሙያው ከበደ ገርባ (ዶ/ር) እንደሚሉት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በርካታ ውጣ ውረዶችን አልፎ መጠናቀቁ የትውልዱ ድል ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሁለተኛው ዙር የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ውሃ ሙሌት ሥነ-ሥርዓት ላይ በታሪክ ውስጥ ማለፍ ዕድል ፣ታሪክ መስራት ደግሞ ድል ነው ይላሉ። የታላቁ ህዳሴ ግድብ የአሁኑ ትውልድ ዕድልና ድል መሆኑንም ነው ያነሱት።
በቤተሰብ የተቀረፀው የእህትማማቾቹ የሃገር ፍቅር ስሜት
Sep 2, 2025 1218
በቤተሰብ የተቀረፀው የእህትማማቾቹ የሃገር ፍቅር ስሜት... ኢትዮጵያ በየዘመናቱ በገጠሟት ችግሮች ሁሉ የበርካታ ጀግኖች መፍለቂያ መሆኗን ያረጋገጠች ሀገር ናት፤ ይህም በአለም አደባባይ ነጻነቷ ተከብሮ፣ ታፍራና ተከብራ እንድትኖር ምክንያት ሆኗል። ኢትዮጵያ በጀግኖች መስዋእትነት ሉአላዊነቷን አስጠብቃ ኖራለች፤ ወደፊትም ነጻነቷ የተከበረ፣ በኢኮኖሚ የበለጸገች፣ ዜጎች ኮርተው የሚኖሩባት ጠንካራ ሀገር ሆና ለመቀጠል በላቀ ትጋት ላይ የምትገኝ ሃገር ናት። ይህ ጽሁፍ በላቀ የሃገር ፍቅር ስሜት ተነሳስተው፤ ለግዳጅ ተዘጋጅተው የራሳቸውን የጀግንነት ህልምና ትልም እውን ለማድረግ በብር ሸለቆ መሰረታዊ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት ሰልጥነው በተመረቁ እህትማማቾች ላይ ያተኩራል። ውልደትና ዕድገታቸው በአዲስ አበባ የሆኑት እህትማማቾቹ ስመኝ ወርዶፋ እና ቃልኪዳን ወርዶፋ በብር ሸለቆ መሰረታዊ ወታደራዊ ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት በመሰረታዊ ወታደርነት ሰልጥነው ተመርቀዋል። ከቤተሰባቸው የወረሱት ከፍተኛ የሃገር ፍቅር ከህጻንነታቸው ጀምሮ በልባቸው እየተብላላ፣ በአዕምሯቸው እየተብሰለሰለና መዳረሻውን እየፈለገ መኖሩን አስረግጠው በኩራት ይናገራሉ። ለሃገር ፍቅር ስሜቱ ምንጭና ጥንስሱም መኖር፣ ማጌጥ፣ መደሰት፣ ማዘን… የሚቻለው በሀገር ላይ ነው፤ ሀገር ስትኖር ሁሉም ህልምና ትልም ይሳካል ተብሎ እየተነገራቸው ማደጋቸው ነው። እህትማማቾቹ ለዘመናት ህልማቸው የሆነውና በልባቸው እየሰረጸ በውስጣቸው እየታገላቸው የሚገኘውን የሃገር ፍቅር ስሜት እንዴት፣ መቼና የት እውን እንደሚያደርጉት ማሰላሰል ከጀመሩ ከራርመዋል። ይህንን ህልማቸውን እውን የሚያደርጉበትን መንገድ በማፈላለግ ላይ እያሉ የሃገር መከላከያ ሰራዊት ማስታወቂያ ማውጣቱን ተመለከትን ይላሉ። ይህም የህልምና ትልም ታሪክ በብር ሸለቆ መሰረታዊ ወታደር ማሰልጠኛ ትምህርት ቤት በመሰልጠን ተመራቂ ሆነው ተገኝተዋል። መሰረታዊ ወታደር ስመኝ ወርዶፋ ከኢዜአ ጋር በነበራት ቆይታ፤ በራሳችን ሙሉ ፈቃድ ወደዚህ ታላቅ ተቋም መቀላቀላችን እኔም ሆንኩ እህቴ በጣም ደስተኛ ነን ስትል በልበ ሙሉነት ገልጻለች።   የሃገር መከላከያ ሰራዊት ያወጣውን ማስታወቂያ እንዳየሁ "ለታናሽ እህቴ ቃልኪዳን የዘመናት ህልማችን እውን የምናደርግበት ታላቅ ብስራት ነው ብዬ ነገርኳት" የምትለው ስመኝ፤ በዚህም ውጥናችንን የምንተገብርበትን መንገድ ለመጀመር አላቅማማንም ብላለች። ምንም እንኳ በልባችን ፀንቶ ከአካላችን ጋር እያደገ የመጣው የላቀ የሀገር ፍቅር ስሜት ሁለታችንንም ገፋፍቶን በጉዳዩ ላይ መክረን እድሉን መጠቀም እንዳለብን መግባባት ላይ ሊያደርሰን ችሏል ትላለች መሰረታዊ ወታደር ስመኝ። በፈቃዳችን ተመዝግበን ወደ ብር ሸለቆ በመምጣት የስነ ልቦና፣ የቴክኒክ፣ የአካል ብቃትና የውጊያ ስልቶችን በተግባርና በንድፈ ሃሳብ ተማርን፤ በዚህም ብዙ ለውጦችን አግኝተንበታል ስትል ገልጻለች። እኔና እህቴ ወደዚህ ከመምጣታችን በፊት ተነጋግረን፣ ተመካክረንና ወስነን ነው የመጣነው ያለችው ስመኝ ፤ አሁን ላይ ስልጠናውን በብቃት አጠናቀን ለቀጣይ ግዳጅ ዝግጁ በመሆናችን ደስተኛ ነን ብላለች። የዘመናዊ መከላከያ ሰራዊት መርህን በመከተልና የሚሰጠንን ተልእኮ በላቀ ብቃት በመፈጸም ሀገራችንና ህዝባችንን ለማገልገል ዝግጁ ነን ስትል ተናግራለች። ሁለታችንም ብር ሸለቆ መሰልጠናችን እየተረዳዳን፣ እየተደጋገፍን፣ እየተመካከርን… ስልጠናውን በከፍተኛ ብቃት ለማጠናቀቅ አስችሎናል፤ ብቸኝነትን በማስወገድ ፈጥነን ተላምደን በሙሉ ልብ ስልጠናውን ለመከታተል አግዞናል ብላለች። የስመኝ ታናሽ እህት የሆነችው መሰረታዊ ወታደር ቃልኪዳን ወርዶፋ በበኩሏ፤ የመከላከያ ሰራዊትን መቀላቀሌ ከልጅነቴ ጀምሮ በውስጤ የኖረውን ፍላጎትና ህልም እንዳሳካ አስችሎኛል ስትል ገልጻለች።   እኔና እህቴ ውስጣችን የነበረውን የሀገር ፍቅር የምንገልጽበት ተቋም ውስጥ በመግባታችን ደስታችን ወደር የለውም ያለችው ቃልኪዳን፤ ከራሳችን በፊት ቅድሚያ ለሃገርና ለሕዝብ የሚለውን የመከላከያ መርህ ለመተግበር ቆርጠን ተነስተናል ብላለች። የሀገር ፍቅር ስሜታችን የመነጨው ከቤተሰብ ነው፤ የመሰረታዊ የውትድርና ስልጠና ወስደን መመረቃችን ትልማችንን እውን ለማድረግ እድል ይፈጥርልናል ብላለች። “የነብርን ጅራት አይዙም፤ ከያዙም አይለቁም” እንደሚባለው ካሁን በኋላ ያገኘነውን እውቀትና ክህሎት ተጠቅመን የሚሰጠንን ተልእኮ በጀግንነት ለመወጣት ቁርጠኛ ነኝ ስትል አንስታለች ቃልኪዳን ። የመከላከያ ሰራዊቱን ስቀላቀል ሀገሬን ለማገልገል ነው፤ የሃገሬንና የሕዝቤን ክብር ለማስጠበቅ እኔ አስፈላጊውን መስዋዕትነት ለመክፈል ተዘጋጅቻለሁ ስትል ገልጻለች። የዘመናዊ ወታደር ስብእናን በመላበስ በሀገራችን ዴሞክራሲ ስር እንዲሰድ፣ የተጀመረው ልማት ዳር እንዲደርስና የሕዝብ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ የድርሻዋን ለመወጣት ቁርጠኛ መሆኗን ተናግራለች። ለዚህም በምትሰማራበት የግዳጅ ቀጠና ሁሉ የሚሰጣትን ተልእኮ ሁሉ በላቀ ተነሳሽነት በመፈጸምና ለተደማሪ ድል በመዘጋጀት ትልሟን በመተግበርና ዳር በማድረስ አሻራዋን ለማስቀመጥ እንደምትተጋም አረጋግጣለች። የእነዚህን ብርቅዬ የሀገር ጀግኖች ታሪክ ለሕዝብ እንዲደርስ ለአብነት ተነሱ እንጂ ሶስት ወንድማማቾች ሆነው የገቡና ሌሎች ታሪኮች ያሏቸው ጀግኖች የመሰረታዊ ውትድርና ተመራቂዎች መኖራቸውን መመልከት ይቻላል። ይህም ኢትዮጵያ የበርካታ ጀግኖች መፍለቂያ ሀገር መሆኗን የሚያሳይ እና ጀግንነት ደግሞ በግለሰብ፣ በቤተሰብ፣ በማህበረሰብና በድምር ውጤት በሀገር የሚገለጥ ሲሆን፤ የእህትማማቾቹ ታሪክ ከቤተሰብ የተገኙ ጀግኖች ናቸው። የጀግንነት ዋናው ምእራፍ ፍላጎት፣ ተነሳሽነት፣ ቁርጠኝትና ዝግጁነት በመሆኑ ሁለቱ ባለታሪኮቻችን እነዚህን ጉዳዮች አሟልተው በግንባር ለሚመዘገበው ድል አኩሪ ተጋድሎ ለመፈጸም የተዘጋጁ ናቸው።
የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል አብዮት
Aug 27, 2025 1114
በሙሴ መለስ/ኢዜአ ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ የአረንጓዴ ኃይል ዋንኛ ማዕከል በመሆን ላይ ትገኛለች። የተፈጥሮ ውበቷን ከኢኖቬሽን ጋር በማስተሳሰር የአየር ንብረትን የማይበክሉ የተለያዩ የታዳሽ ኃይል አማራጮችን እየተጠቀመች ይገኛል። አዲስ አበባ ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ለማስተናገድ ዝግጅቷን አጠናቃ እንግዶቿን እየተጠባበቀች ነው። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ስራ በጉባኤው ከምታቀርባቸው ተሞክሮዎች መካከል ይጠቀሳል። ኢትዮጵያ ከውሃ፣ ከፀሐይ፣ ከነፋስ፣ ከእንፋሎት ሃይል፣ ባዮማስ ከእንስሳትና እጽዋቶች ተረፈ-ምርት ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅም አላት። ይህም የሚያሳየው አብዛኛውን የኤሌክትሪክ ኃይል የምታገኘው ከታዳሽ የኃይል ምንጮች መሆኑን ነው። ኢትዮጵያ ከጂኦተርማል 10 ሺህ ሜጋ ዋት ከንፋስ ኃይል ደግሞ 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ሀይል የማመንጨት እምቅ አቅም አላት። ግንባታው የተጠናቀቀው እና 5 ሺህ 200 ሜጋ ዋት የሚያመነጨው የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብም ከብክለት ነጻ የኃይል ምንጭ ከመሆን ባለፈ ለሀገሪቷ ኢኮኖሚ አስተዋጽኦ እያደረገ ይገኛል። መንግስት የሀገሪቱን የኃይል እጥረት ለመቅረፍ በዋና ዋናዎቹ የወንዞች ተፋሰሶች የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ፕሮጀክቶችን በማልማት ላይ ይገኛል። በ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅዷ ኢትዮጵያ የምታመነጨውን የኃይል መጠን አሁን ካለበት 4 ሺህ 818 ሜጋ ዋት ወደ 17 ሺህ ሜጋ ዋት ለማሳደግ ግብ ተቀምጧል። የተሻሻለው የኢነርጂ ፖሊሲዋም ሀገራዊ፣ ቀጣናዊና ዓለም አቀፍ ነባራዊ ዕውነታ መሰረት ያደረገ እና ጎረቤት ሀገራትን በኃይል መሰረተ ልማት ለማስተሳሰር ያለመ ነው። ይህንንም እውን ለማድረግ በመንግስት ከሚለሙት የኃይል ምንጮች በተጨማሪ በግሉ ዘርፍ ኃይል ተመርቶ የኃይል አቅርቦቱ እንዲሻሻልና ዘላቂ እንዲሆን አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡ ይህንንም እውን ለማድረግ በ2009 ዓ.ም በገንዘብ ሚኒስቴር ስር የመንግስትና የግሉ ዘርፍ አጋርነት ፕሮጀክት በአዋጅ ቁጥር 1076/2018 ተመስርቷል። በዚህ የመንግስትና የግሉ ዘርፍ አጋርነት ስምንት የፀሐይ ኃይል፣ አምስት የሃይድሮ ኤሌክትሪክ እና አምስት የንፋስ ኃይል ፕሮጀክቶችን ለማልማት እየተሰራ ይገኛል። ከስምንቱ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች እስከ 750 ሜጋ ዋት ኃይል ለማግኘት መታቀዱን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መረጃ ያመለክታል። ጋድ 1 እና 2፣ ዲቼቶ፣ ወራንሶ፣ ሁመራ፣ ወለንጪቲ፣ መቀሌ፣ ሁርሶ እና መተማ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶቹ ናቸው። አዳማ አንድ፣ አዳማ ሁለት፣ አይሻ ሁለት እና አሸጎዳ ከንፋስ ኃይል ፕሮጀክቶቹ መካከል ይጠቀሳሉ። የእንፋሎት (ጂኦተርማል) ኃይልን በተመለከተም በመንግስትና የግሉ ዘርፍ አጋርነት ፕሮጀክት ኮርቤቲ ከሚባል የግል አልሚ ጋር መንግስት ተዋውሎ ድርጅቱ የሚያመርተውን 150 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ለኢትዮጵያ ለማቅረብ እየሰራ ይገኛል። በአጠቃላይ በተለያዩ የኢነርጂ አማራጮች የኢትዮጵያን የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነት ሽፋንን 54 በመቶ ማድረስ መቻሉን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። በብሔራዊ ኤሌክትሪፊኬሽን ፕሮግራም አማካኝነት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2030 65 በመቶ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከብሔራዊ የኃይል ቋት እንዲሁም ቀሪው 35 በመቶ ከኃይል ቋት ውጭ ባሉ ቴክኖሎጂዎች ተደራሽ የማድረግ እቅድ ተይዟል። ኢትዮጵያ ከራሷ አልፋ ለምስራቅ አፍሪካ ሀገራት እያቀረበች ያለው አረንጓዴ የኃይል አማራጭ የአየር ንብረት ተጽእኖን ለመከላከል እና ከባቢ አየርን ለመጠበቅ ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው። የተሻሻለው የኢነርጂ ፖሊሲዋም ሀገራዊ፣ ቀጣናዊና ዓለም አቀፍ ነባራዊ ዕውነታ መሰረት ያደረገ እና ጎረቤት ሀገራትን በኃይል መሰረተ ልማት ለማስተሳሰር ያለመ ነው። በርግጥ ከሕዳሴው ግድብ ባሻገር ሌላው ከአፍሪካ ግዙፍ ፕሮጀክቶች አንዱ የሆነው የኮይሻ ኃይል ማመንጫም ለቀጣናዊ ትስስር መፋጠን ሌላው እድል ነው። በጥቅሉ ኢትዮጵያ ለጎረቤት አገራት የምታቀርበው የኤሌክትሪክ ኃይል የሀገራት ኢኮኖሚ ትብብር የሚያጠናክር እና የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት የማስተሳሰር ጽኑ ፍላጎት ማሳያ ነው። በተጨማሪም በቀጣናው ዘላቂ የኤሌክትሪክ ገበያ ልማትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ክፍለ አሕጉራዊ ጥረት ነው። ጥረቱ የምሥራቅ አፍሪካ የሃይል ቋት (The Eastern Africa Power Pool-EAPP) በቀጣናው ሀገራት መካከል ድንበር ተሻጋሪ የሃይል ንግድ እና የሃይል መስመር ትስስርን ለማሳለጥ እኤአ በ2005 የተቋቋመ ተቋም ግብ እውን ከማድረግ ባለፈ አሕጉራዊ ምጣኔ ሃብታዊ ትስስርን ያፋጥናል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኢነርጂ አብዮት የአየር ንብረት ለውጥ የመከላከል ስራ እና የደን ልማትን የሚያግዝ ነው። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ እየተቃረበ ባለበት ወቅት ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኃይል አሻራውን ለአፍሪካ ለማሳየት ተዘጋጅታለች። አረንጓዴ የኃይል አማራጮች ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት የማይበገር ኢኮኖሚ መገንቢያ ዋና ምሰሶዎች መካከል ይጠቀሳል።
የኢትዮጵያ የካርቦን ገበያ፤ፍትሃዊ የአየር ንብረት ፋይናንስ አቅርቦት ማግኛ አማራጭ ---
Aug 26, 2025 1047
ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል። “ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፤ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" የጉባኤው መሪ ሀሳብ ነው። ከጉባኤው አጀንዳዎች መካከል የአፍሪካ የካርቦን ሽያጭ ይገኝበታል። የካርቦን ንግድ ማለት የካርቦን ዳይኦክሳይድ እና ሌሎች የአየር ንብረት ለውጥን የሚያስከትሉ ጋዞችን ልቀትን ለመቆጣጠር የሚደረግ የገበያ ዘዴ ነው። ልክ እንደ ሌሎች ምርቶች ሁሉ የካርቦን ልቀትን የመገበያያ ዕቃ አድርጎ ይቆጥረዋል። መንግስታት ወይም ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ኩባንያዎች ወይም ተቋማት ሊለቁት የሚችሉትን ከፍተኛውን የካርቦን መጠን ይወስናሉ።ይህ መጠን “የልቀት ጣሪያ” (Emission Cap) ይባላል። ከዚያም እያንዳንዱ ኩባንያ ይህን ያህል ካርቦን የመልቀቅ “ፈቃድ” ወይም “ክሬዲት” (Credit) ይሰጠዋል። ካርቦን ክሬዲት፦ ኩባንያዎች እንደ ደን ልማት ወይም የታዳሽ ኃይልን በመሳሰሉ ፕሮጀክቶች ላይ ኢንቨስት በማድረግ ብድር የሚያገኙበት ስርአት ነው። የካርቦን ንግድ ሀገራት፣ኩባንያዎች እና ግለሰቦች በተገዢነት እና በፈቃደኝነት ላይ ተመስርተው የሚያከናወኑት ነው። አፍሪካ በዓለም ደረጃ ወደ ከባቢ አየር በሚለቀቀው በካይ ጋዝ ልህቀት ከአራት በመቶ ያነሰ ድርሻ ቢኖራትም የአየር ንብረት ለውጥ ከፍተኛ ዳፋ ተሸካሚ አህጉር ሆናለች። የካርቦን ገበያ ለአፍሪካ ሀገራት የአየር ንብረት ፋይናንስ እንዲያገኙ ከማድረግ ባለፈ ለስራ እድል እና ለብሄራዊ አየር ንብረት ለውጥ ማጣጣሚያ እቅዶች ትግበራ የበኩሉን ሚና እየተጫወተ ይገኛል። የአፍሪካ ሀገራት በ2015 ዓ.ም በግብጽ ሻርም አል ሼክ በተካሄደው 27ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንበረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ-27) የአፍሪካ ካርቦን ገበያ ኢኒሼቲቭ ይፋ አድርገዋል። በኢኒሼቲቩ አማካኝነት አፍሪካ በዓመቱ በ300 ሚሊዮን የካርቦን ክሬዲት ስድስት ቢሊዮን ዶላር ገቢ ለማግኘት አቅዳለች። እ.አ.አ በ2030 በካርቦን ንግድ ለ30 ሚሊዮን ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ውጥን ተይዟል። የካርቦን ገበያ በአፍሪካ ሀገራት ተስፋ ሰጪ እድገት እያሳየ ይገኛል። ኢትዮጵያን ጨምሮ ኬንያ፣ ጋና፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሩዋንዳ እና ሴኔጋል የካርቦን ገበያ የአሰራር ማዕቀፎችና ግቦች አዘጋጅተው እየሰሩ ይገኛል። የአፍሪካ ልማት ባንክም የካርቦን ገበያ የፋይናንስ አማራጭ በማዘጋጀት ሀገራት ማዕቀፎች እንዲቀርጹና የካርቦን ክሬዲት በአፍሪካ የአክሲዮን ገበያዎች ውስጥ እንዲካተቱ አድርጓል። የአፍሪካ ሕብረት የልማት ኤጀንሲ (አውዳ-ኔፓድ) በአህጉሪቷ የካርቦን ገበያ ቀረጻ፣ ትግበራ እና የግብይት ስርዓቱን የሚወስን “African Gold Standard” የተሰኘ የአሰራር ማዕቀፍ አዘጋጅቶ እየተገበረ ይገኛል። ማዕቀፉ የካርቦን ገበያ ማህበረሰቦች ካርቦንን በማመቅ ስራቸው ተጨባጭ ተጠቃሚነታቸው እንዲረጋገጥና ለብዝበዛ እንዳይጋለጡ ክትትልና ድጋፍ የሚደረግበት መንገድ ነው። የአየር ንብረት ጉባኤውን የምታዘጋጀው ኢትዮጵያ በካርበን ገበያ ተጠቃሚነቷን ለማረጋገጥ እየሰራች ትገኛለች። ኢትዮጵያ ሙቀት አማቂ ጋዞች ልቀት ቅነሳና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የ10 ዓመት መሪ የልማት እቅድ ቀርጻ ስትራቴጂካዊ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ እንደሆነች የፕላንና ልማት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። የእርምጃዎቹ አንድ አካል የሆነው የካርቦን ግብይትን በውጤታማነት ለመምራትና ተጠቃሚ ለመሆን ብሔራዊ የካርበን ግብይት ስትራቴጂ አዘጋጅታለች። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር በኢትዮጵያ የካርቦን ግብይት ስትራቴጂ የመጨረሻ ረቂቅ ግምገማ እና የካርቦን ገበያ የህግ ማዕቀፍ የህግ ክፍተት ዳሰሳ ጥናት ሪፖርት (Validation Worksop on draft Ethiopia’s National Carbon Market Strategy and Consultation on the Legal Gap Analysis Report) ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በግንቦት ወር 2017 ዓ.ም በቢሾፍቱ አካሄዶ ነበር። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ስትራቴጂውን በፍጥነት ወደ ስራ ለማስገባት ከስትራቴጂ ዝግጅቱ ጎን ለጎን የካርቦን ገበያ ሊመራበት የሚችል የህግ ማእቀፍ ለማዘጋጀት የህግ ክፍተት የዳሰሳ ጥናት መካሄዱን ገልጸዋል። የማዕቀፉ ዓላማ በኢትዮጵያ በአግባቡ ተግባራዊ ሊደረግ የሚችል የህግ ማዕቀፉን በፍጥነት አዘጋጅቶ በማጸደቅ የካርቦን ግብይት ላይ በንቃት እና የኢትዮጵያን ተጠቃሚነት ባረጋገጠ መልኩ መሳተፍ እንደሆነ ተናግረዋል። በመድረኩ ላይ የካርቦን ገበያ ልማት ስትራቴጂ ረቂቅ ሰነድ እና የካርቦን ገበያ ንግድ የህግ ማዕቀፍ ዳሰሳ ጥናት ሰነድ ግብአቶችን አካቶ በማዳበር ያሉትን ሂደቶች በማለፍ በቅርብ ጊዜ ወደ ስራ እንዲገባ አቅጣጫ ተሰጥቷል። ብሔራዊ የካርቦን ገበያ ሽያጭ ስትራቴጂ መዘጋጀቱ ኢትዮጵያ በደን ልማት፣በትራንስፖርት፣ በቆሻሻ አወጋገድና በኃይል አማራጭ ልማት ላይ በምታበረክተው ልክ ተጠቃሚ የሚያደርጋት መሆኑን ሚኒስቴሩ ገልጿል። በዚህም ሙቀት አማቂ ጋዞችን በመቀነስ፣ አረንጓዴ ኢኮኖሚ በማሳለጥና የዜጎችን ተጠቃሚነት በማሳደግ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስራን ለማገዝ ጉልህ ፋይዳ ያለው መሆኑን አመልክቷል። ኢትዮጵያ ከኖርዌይ በየካቲት ወር 2016 ዓ.ም የተፈራረመችው የ75 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የካርቦን ሽያጭ ስምምነት በካርቦን ግብይቱ እያገኘች ያለውን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት የሚያሳይ ነው። እ.አ.አ እስከ 2026 ድረስ የሚቆየው ስምምነት ከካርበን ሽያጭ የሚገኘውን ገቢ እንደ ሀገር የተሰሩ የአረንጓዴ ልማት ስራዎችን ለማጠናከር እንዲሁም አዳዲስ የደን ልማት ስራዎችን ለመስራት ይውላል። በባሌና ምዕራብ አርሲ ጥብቅ ደኖች ሲተገበር በቆየው የበካይ ጋዞች ቅነሳና የደን ጭፍጨፋን የመቀነስ ፕሮጀክት (ሬድ ፕላስ) አማካኝነት እየተከናወነ ያለው የካርቦን ንግድ በሚሊዮኖች ብር የሚቆጠር ብር ገቢ እየተገኘበት ነው። ፕሮጀክቱ በመተግበሩ ጉዳት ይደርስበት የነበረው የደን ሀብት መጠበቅ እና የካርቦን ጋዝ ልቀትን ማስቀረት ተችሏል። ኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ የካርቦን ገበያ ተጠቃሚነቷን ለማሳደግ በሀገሪቷ የተለያዩ ጥብቅ ደኖች ካርቦኖችን በማከማቸት ገቢ እንዲገኝ እየሰራች ነው። የካርቦን ግብይት የኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ የማግኘት አማራጭ በማስፋት ረገድ ቁልፍ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ በመገንባት እና የካርቦን ገበያ የአሰራር ማዕቀፍ በመዘርጋት እያከናወነች ያለው ስራ ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው። በሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤም በካርቦን ገበያ ያላትን ተሞክሮ ታቃርባለች ተብሎ ይጠበቃል። በጉባኤው ላይ የካርቦን ገበያ የበካይ ሀገራት እና ኩባንያዎች የገንዘብ መክፈያ ዘዴነት ወጥቶ በአፍሪካውያን ባለቤትነት እንዲመራ መሪዎች ጠንካራ ጥሪ እንደሚያቀርቡ ይጠበቃል። አፍሪካ በጉባኤው ላይ ጠንካራ የካርቦን ገበያ አስተዳደር ስርዓት መገንባት፣የካርቦን ክሬዲት ሽያጭ ላይ የሚያጋጥሙ የክፍያ ክፍተቶች ዘላቂ መፍትሄ እንዲያገኙ ማድረግ፣ የማህበረሰብ ተጠቃሚነትን የበለጠ ማረጋገጥ፣ ተጠያቂነትን ማስፈን እና ፍትሃዊ ገቢ ማግኘት ላይ ለውጥ የሚያመጡ ውሳኔዎችን ማሳለፍ እንዳለባቸው የዘርፉ ባለሙያዎች ይመክራሉ። የካርቦን ገበያ በተገቢው ሁኔታ የሚፈጸም እና የአፍሪካን ባለቤትነት የሚያረጋግጥ ከሆነ ለአህጉሪቷ ዘላቂ የፋይናንስ አማራጭ፣ አይበገሬነትን ለመገንባት እና ዘላቂ እድገትን ለማምጣት ወሳኝ ሚና ይጫወታል።
አሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል- የልጃገረዶች የባህል ፈርጥ
Aug 24, 2025 750
አሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል- የልጃገረዶች የባህል ፈርጥ በእንግዳው ከፍያለው የነሃሴ ወር የልምላሜ ምልክት ነው። ከሰኔ አጋማሽ ጀምሮ የሚዘንበው ዝናብ ፍሬው የሚታየው በነሃሴ ወር ምድርን በሚያለብሰው ቡቃያና የሳር ልምላሜ ነው። በዚህ ወር ሌት ከቀን የሚጥለው ዝናብ፣ በነፋስ የሚታገዘው ውሽንፍር፣ ውርጩና ቁሩ ሳይበግራቸው ልጃገረዶች ይሰባሰባሉ። የአሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል በዓልን ለማከበር በእድሜ እኩያቸውና እንደየሰፈር ቅርበታቸው ቡድን ይመሰርታሉ።   ቡድን መመስረት ብቻ ሳይሆን “አሸንድዬ አኽ፤ አሸንዳ ሆይ፤ እሽ እርግፍ አትይሞይ፤…” የሚለውን የበዓሉን ማድመቂያ ጭፈራ መለማመድ ይጀምራሉ። ከልምምዱ ጎን ለጎንም ለጆሯቸው ጉትቻ፣ ለአንገታቸው ድሪ፣ ማርዳ፣ ጠልሰምና ማሰሪያ የተለያየ ቀለም ያላቸው ክሮችን በመሰብሰብ ያዘጋጃሉ። ለእጃቸው አምባር፣ ለእግራቸው አልቦና ሌሎች ጌጣጌጦችን ያፈላልጋሉ፤ ያሰባስባሉ፣ ያመቻቻሉ። ጌጣጌጦቹ ከእናቶቻቸው፣ ታላቅ እህቶቻቸውና ሌሎች ቤተሰቦችም ጭምር የሚሰበሰቡ ናቸው። አዲስ የሚገዛ ገዝቶ ወይም ለክት የተቀመጠውን በማውጣት አልባሳት ያዘጋጃሉ። በበዓሉ ዋዜማ ለባህላዊ ጭፈራው ስያሜ መነሻ የሆነው “አሸንዳ” እየተባለ የሚጠራውን ረጃጅም ቅጠል ያለውን ተክል በማምጣት በወገብ ለማሰር በሚያመች መልኩ ተጎንጉኖ በጓሮ ጤዛ በያዘ ሳር ተሸፍኖ እንዲያድር ይደረጋል። ይህ የሚደረገው ጠንዝሎ እንዳይበጣጠስ ነው።   የጸጉር ስሬትም ምን ዓይነት መሆን እንዳለበት፤ ጥሩ ጸጉር ሰሪ ማን እንደሆነች በመነጋገር ቀድመው ወረፋ ያስይዛሉ። ለጸጉር ሰሪዋም በአይነትም ሆነ በብር ክፍያ ይዘጋጃል፤ ቀደም ሲል በነጻ እንደነበርም ይነገራል። ይህ ሁሉ ዝግጅት የልጃገረዶች በዓል የሆነውን የአሸንድዬ፣ ሻደይ፣ ሶለል በዓል በጋራ ለማክበር ነው። ዝግጅቱን ለሚያይ ሰው “ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ፤ ይበጣጠስ” የሚለውን የሀገሬውን ብሂል ለአሸንድዬ ያልሆነ ቀሚስ ... የተባለ ነው የሚያስመስለው። ማህበረሰቡ በየቤቱ ምግብና መጠጥ በማዘጋጀት እርስ በእርስ በመጠያየቅ የሚያጅብበት በዓልም ነው። ድፎ ዳቦ፣ ሙልሙል ዳቦ፣ ጠላ፣ ጠጅና ሌሎች የምግብና የመጠጥ አይነቶች በየቤቱ ማዘጋጀት የተለመደ ነው። ልጃገረዶች በየቤቱ እየዞሩ ሲጨፍሩ አንዱ ስጦታ ሙሉሙል ዳቦ ይሆናል ማለት ነው። በዓሉ የሚከበርባቸው አካባቢዎችም በሰሜን ወሎ ዞን ላሊበላ፣ ቡግና፣ መቄት፣ ግዳን፣ ቆቦ፣ ጉባላፍቶና መርሳ አካባቢዎች ሲሆን በዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር በሁሉም ወረዳዎች በድምቀት ይከበራል። በዓሉ ከጥንት ጀምሮ በአካባቢው ማህበረሰብ ዘንድ በድምቀት የሚከበር ነው። ከነሃሴ 16-21 በሚከበረው የበዓል ሳምንት ሴት ልጆች ከብት እንዲጠብቁ አይገደዱም፣ ሌላ ስራም እንዲሰሩ አይጠየቁም። ምክንያቱም እለቱ ለእነርሱ የነፃነት ቀናቸው ነውና። በዓሉ በልጃገረዶች ጭፈራ ብቻ የሚከበር ሳይሆን በታዳጊና ወጣት ወንዶች ጅራፍ ግርፊያና ማጮህ ታጅቦ የሚከበር ነው። የአሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል በዓል በአካባቢው ባህል ተጨማሪ እሴት ያለው በዓል ነው። ለመተጫጨት ምቹ አጋጣሚ የሚፈጥር በዓልም ነው። በዓሉ ከመተጫጨትም ባለፈ ለሌሎች ማህበራዊ ትስስሮች ፋይዳው የጎላ ነው። ልጃገረዶች በመሰረቱት ቡድን አምረው ለብሰውና ከጸጉር እስከ እግራቸው በተለያዩ ጌጣጌጦች ተውበው በዓሉን እያዜሙ ያከብራሉ። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በዓሉ ከሰፈር ወጥቶ ትልቅ ትኩረትም አግኝቶ በየአደባባዮች መከበር ይዟል። በዚህም የውጭና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎችን ቀልብ እየሳበ በአካበቢው ከሚገኙት ታሪካዊ የመስህብ ሃብቶች በተጨማሪ አዲስ የመስህብ ምንጭ እየሆነ መጥቷል። ይህንን ድንቅና ታሪካዊ እሴት በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባሕል ድርጅት /ዩኒስኮ/ በማስመዝገብ ኢትዮጵያን እንዲያስተዋውቅና ዓለም አቀፍ የቱሪዝም መስህብ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። የዘንድሮው የአሸንድዬ፣ ሻደይና ሶለል በዓል ታሪካዊና ባህላዊ እሴቱን ጠብቆ በደማቅ ስነ ስርአት ተከብሯል። የበዓሉ አከባበር ባህላዊ እሴቱን አጉልቶ በማሳየት፣ ለሀገር ገጽታ ግንባታ፣ ለቱሪዝም ሃብት ምንጭነትና ለኢኮኖሚ ማንሰራራት የላቀ ፋይዳ እንዳለውም ይታመናል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም