ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በአዲሱ በጀት አመት ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ተጠናክሮ ይቀጥላል- የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Jul 13, 2025 23
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦በ2018 በጀት አመት ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ተናገሩ። የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ የኢንተርፕራይዞች ምስረታ እና የሰልጣኞች ምዝገባ በኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት ተግባራዊ የማድረግ ሥራ እንደሚቀጥልም ሚኒስትሯ ገልጸዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የዘርፉ የክልልና ከተማ አስተዳደር አመራሮች የኢንተርፕርነርሺፕ ስልጠና እና ዓመታዊ የዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚልን ጨምሮ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የተጠሪ ተቋማት ኃላፊዎች፣ የክልልና የከተማ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊዎች፣ የፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዲኖች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በመድረኩ እንደተናገሩት፤ ባለፉት አመታት በተቋም ግንባታ፣ በክህሎት ልማት፣ በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በአሠሪና ሠራተኛ አበረታች ተግባራት ተከናውነዋል። የተቋም ግንባታው ሀገር የጀመረችውን ሁለንተናዊ ብልፅግና ለማረጋገጥ በሚችል መልኩ መገንባቱን ጠቅሰው፤ የአሠራር ሥራዓቶችን የማሻሻል እና በቴክኖሎጂ የማዘመን ሥራም በትኩረት መሠራቱን ገልጸዋል። ይህም በ2018 በጀት አመት ይበልጥ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነው ሚኒስትሯ ያስታወቁት። በክህሎት ልማት ረገድም በተጠናቀቀው በጀት አመት አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ጠቅሰው፤ የሰው ሀብት ልማት ሥራም ገበያ እና ፍላጎትን መሠረት በማድረግ መሰራቱን ተናግረዋል። የሥራ እድል ፈጠራ ቁጥር ሪፖርት ጥራቱን የጠበቀ ለማድረግም የኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት ተግባራዊ መደረጉን ገልጸዋል። ህጋዊ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪትን ተግባራዊ ለማድረግ፣ ለኢንተርፕራይዞች የገበያ ትስስር ለመፍጠርና ፋይናንስን ጨምሮ አስፈላጊ መንግስታዊ ድጋፎችን ለማቅረብ የሚያስችል እንደሆነም ተናግረዋል። በ2018 በጀት አመት ሁሉም የዘርፉ ተቋማት የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ የኢንተርፕራይዞች ምስረታ እና የሰልጣኞች ምዝገባ በኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት የማካሄድ ሥራን አጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ሚኒስትሯ አስገንዝበዋል። በሀገር ውስጥ፣ በውጭ ሀገር እና በርቀት ሥራ ዕድል ፈጠራ አበረታች ስራዎች መሰራቱን ጠቅሰው፤ በአዲሱ በጀት አመትም የበለጠ ስኬት ለማስመዝገብ ርብርብ እንደሚደረግ አመላክተዋል።
በዞኑ የህብረት ስራ ማህበራትን አቅም በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው
Jul 13, 2025 37
ደብረማርቆስ ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን የህብረት ስራ ማህበራትን አቅም በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ። የዞኑ ግብርና መምሪያ 17 የእርሻ ትራክተሮችና ኮምባይነሮችን ለሁለገብ የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበራትና ባለሀብቶች ዛሬ አስረክቧል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኑርልኝ ብርሃኑ እንዳሉት በዞኑ የህብረት ስራ ማህበራትን አቅም በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው። የምርታማነት ማደግ የአርሶ አደሩን የኑሮ ደረጃ ከማሻሻል ባለፈ ገበያን በማረጋጋት የዋጋ ንረትን በመቀነስ ረገድ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። የዞኑን የምርታማነት አሁን ካለበት ለማሳደግ የሜካናይዜሽን ግብርናን ማስፋፋትና ተደራሽ ማድረግ የህልውና ጉዳይ ሊሆን ይገባል ያሉት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበበ መኮንን ናቸው። ለዚህም የክልሉ መንግስት ባደረገው ድጎማ ዘጠኝ ትራክተሮችና ስድስት ኮምባይነሮችን ለሁለገብ የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበራት ድጋፍ ማድረግ እንደቻለም ተናግረዋል። በተጨማሪም በረጅም ጊዜ ክፍያ ለሁለት ባለሀብቶች ሁለት ትራክተሮች ቀርበው ርክክብ መደረጉን ገልጸዋል። የክልሉ ህብረት ስራ ማህበራት ኤጀንሲ አማካሪ አቶ ሃይለ ልኡል ተስፋ በበኩላቸው የሜካናይዜሽን ግብርና ተደራሽነት እንዲሰፋ አልሚ ባለሃብቶችን ከቀረጥ ነጻ እንዲያስገቡ እና ብድር እንዲያገኙ የሚደረገው ጥረት እንዲጠናከር ጥሪ አቅርበዋል። በተጨማሪም ሁለገብ የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበራት በራሳቸው አቅም የሜካናይዜሽን እርሻን እንዲያስፋፉ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግላቸውም ገልፀዋል። በእነማይ ወረዳ የልምየት የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበር አባል አርሶ አደር ብርቄ ጸጋዬ እንዳሉት ''የሜካናይዜሽን አቅርቦት ድጋፍ መደረጉ በስራችን እንድንበረታ የሚያደርግ ነው'' ብለዋል። ከዚህ ቀደም ሜካናይዜሽን ባለመኖሩ በባህላዊ አስተራረስና የምርት አሰባሰብ ጊዜያቸውን ያባክኑ እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ግን በአካባቢው የሜካናይዜሽን እርሻ መጀመሩ የአርሶ አደሩን ችግር ያቃልላል የሚል ተስፋ ማሳደሩንም አርሶ አደር ብርቄ ተናግረዋል። በዞኑ ለምርት ዘመኑ ከ642 ሺህ ሄክታር በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን በዚህም ከ25 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚገኝም ተገልጿል። በምስራቅ ጎጃም ዞን በሰብል ከሚሸፈነው መሬት 58 በመቶ የሚሆነው በትራክተር ለመታረስ ምቹ መሆኑም ከዞኑ ግብርና መምሪያ የተገኘው መረጃ ያስረዳል።
ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራቾች በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት እያሳዩ ነው
Jul 13, 2025 42
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራችና ሻጭ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ምርታቸውን ለማቅረብና በዘርፉ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ፍላጎት እያሳዩ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን ገለፁ። በየዓመቱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን የሚገጣጥሙና ለሽያጭ የሚያቀርቡ ተቋማት ቁጥር እያደገ መምጣቱንም ገልፀዋል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን ለኢዜአ እንደገለጹት በአገሪቱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለማስፋፋትና በዘርፉ ያለውን ኢንቨስትመንት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው። የነዳጅ ኃይል ጥገኝነት ለመቀነስና የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ዘርፉን አገሪቱ ካላት እምቅ የታዳሽ ሃይል ሀብት ተጠቃሚ ለማድረግ አበረታች ስራዎች መጀመራቸውን ተናግረዋል። ሀገር አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከሪካሪዎች ስትራቴጂን ተግባር ላይ በማዋል ተግባራዊነቱን ለማፋጠንና ኢንቨስትመንቱን ሳቢ ለማድረግ የሚረዱ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። መንግስት በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ የመቀየር እንዲሁም የነዳጅ አጠቃቀምንና ብክለትን በሚቀንሱ ቴክኖሎጂዎች ላይ የሚሰሩ ስራዎችን እያበረታታ መሆኑንም አስታውቀዋል። በነዳጅ የሚሰሩ የቤት አውቶሞቢሎች ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ እገዳ መጣሉን አንስተው በአለም ገበያ ተደራሽ ያልሆኑ ከባድ ተሽከርካሪዎችና መሳሪያዎች በእገዳው አለመካተታቸውን ጠቅሰዋል። በቅርቡ ከሁለት እግር ጀምሮ እስከ ከተማ አውቶብስ ያሉና በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን በሀገር ውስጥ መገጣጠም መከልከሉን አንስተዋል። በዘርፉ ለተሰማሩ ባለሃብቶች የተለያዩ ማበረታቻዎች በፖሊሲ፣ ስትራቴጂና በመመሪያ ተደግፈው ተግባራዊ በመደረጋቸው በርካታ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቁጥር ከ115 ሺህ በላይ እንዲሁም የኤሌክትሪክ ተሽከሪካሪ መገጣጠሚያ ድርጅቶች ቁጥር ከ15 በላይ መድረሱን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ለዘርፉ የሰጠችውን ትኩረት ተከትሎ አሁን ላይ በርካታ ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራቾችና ሻጮች በዘርፉ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ሰፊ ፍላጎት እያሳዩ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በአሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚሰጥ የከተማ የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎትን ለማስፋፋት የሚረዱ ስራዎች በመንግስትና በግል አጋርነት መጀመራቸውን ጠቅሰዋል። በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ባትሪ መሙያ ቋሚ ጣቢያዎች ቁጥር ከ90 እንደማይበልጥ አንስተው ይህንን ለማሳደግ የመንግስት የልማት ድርጅቶችና የግል ባለሀብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ መንግሥት ተግባራዊ ያደረጋቸው የኢኮኖሚ ሪፎርሞች የህንድ ባለኃብቶች በኢትዮጵያ ያላቸው ተሳትፎ እንዲጨምር ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው
Jul 13, 2025 64
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ መንግሥት ተግባራዊ ያደረጋቸው የኢኮኖሚ ሪፎርሞች የህንድ ባለኃብቶች በኢትዮጵያ ያላቸው ተሳትፎ እንዲጨምር ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው ሲሉ በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ገለጹ። የኢኮኖሚ ሪፎርሙ መንግሥት የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ለማሳደግ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑንም አምባሳደሩ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በኢትዮጵያ በተለያዩ መስኮች ተግባራዊ የተደረጉ የኢኮኖሚ ሪፎርሞች በህንድ እና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግሩ ናቸው። መንግስት ከወሰዳቸው የሪፎርም እርምጃዎች መካከል የውጭ ምንዛሬ ተመን በገበያው እንዲወሰን መደረጉ፣ የውጭ አገር ዜጎች የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለቤት መሆን የሚችሉበት አዋጅ መጽደቁ የውጭ ባለኃብቶችን ተሳትፎ የሚያሳድግ ትልቅ እርምጃዎች ናቸው ብለዋል። ከዚህ ቀደም ለውጭ ባለኃብቶች ዝግ የነበሩ የኢኮኖሚ መስኮች ክፍት መደረጋቸው የውጭ ባለኃብቶች በኢትዮጵያ እንዲሰማሩ መፈቀዱ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን የሚያበረታታ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የህንድ ኩባንያዎችም በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት ማሳየታቸውን ጠቁመው፤ በማዕድን፣ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በባንክና ፋይናንስ፣ የካፒታል ገበያ በርካታ ቁጥር ያላቸው የህንድ ባለኃብቶች ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት እንዳላቸው ጠቁመዋል። በግብርናው መስክም ኢትዮጵያ ውጤታማ ለመሆን የሚያስችሉ እምቅ አቅም እንዳላት የገለጹት አምባሳደሩ፤ ሰፊ የሚታረስ መሬት፣ የውኃ ኃብት የሰው ኃይልና ሌሎች የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት የሚስቡ አቅሞች መሆናቸውን ተናግረዋል። የህንድ ባለኃብቶችም በግብርናው ዘርፍ በሰብል ልማት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በአበባ ልማት እንዲሁም ለመድሃኒት ምርት ግብዓት የሚውሉ ተክሎች ልማት ላይ የመሳተፍ ፍላጎት እንዳላቸውም አንስተዋል። በንግድና በኢንቨስትመንት በኩልም በአገራቱ መካከል ያለውን ግንኙነት ወደ ስትራቴጂያዊ አጋርነት ማሳደግ እንደሚያስፈልግ ጠቁመው፤ በዚህም ላይ እየተሰራ ነው ብለዋል። በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የንግድ ልውውጥ ለማሳለጥ የሚረዳ የጋራ የንግድ ኮሚሽን መቋቋሙን ገልጸው፤ ኮሚሽኑ ግንኙነቱን በሚያሳድጉ ጉዳዮች ላይ እየተወያየ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ በየዘርፉ ያሉ የኢንቨስትመንት አማራጮች ላይ ከሚመለከታቸው አካላት ተገቢውን ገለጻ እያገኘን ነው ያሉት አምባሳደሩ በአገራቱ መካከል ያለው ግንኙነት እየተጠናከረ መምጣቱን አብራርተዋል። የብሪክስ የትብብር ማዕቀፍም አገራቱ ግንኙነታቸውን ይበልጥ እንዲያሳድጉ ዕድል መፍጠሩን አስረድተዋል።
በመዲናዋ በከተማ ግብርና ከ159 ሺህ በላይ አዳዲስ ተጠቃሚዎች ወደ ስራ ገብተዋል
Jul 13, 2025 67
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦በ2017 በጀት ዓመት ከ159 ሺህ በላይ አዳዲስ ተጠቃሚዎች ወደከተማ ግብርና ስራ መግባታቸውን የአዲስ አበባ የአርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽን ገለጸ። የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር መሰለ አንሸቦ ለኢዜአ እንደገለጹት የከተማ ግብርና በተለይ የሌማት ትሩፋት መርኃ ግብር ከጊዜ ወደ ጊዜ ውጤታማነቱ እየጨመረ መጥቷል። ኮሚሽኑ በበጀት አመቱ በዘርፉ ለተሰማሩ ነዋሪዎች አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ማድረጉን ገልፀው፤ ቀደም ብለው ወደ ዘርፉ የገቡትን አጠናክሮ የማስቀጠልና አዳዲስ ስራ ጀማሪዎችን ወደ ስራ የማስገባት ስራ በትኩረት መስራቱን አንስተዋል። በኅብረተሰቡ ዘንድ በትንሽ ሥፍራ የከተማ ግብርናን ተግባራዊ በማድረግ ከራስ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ትርፋማ መሆን እንደሚቻል የግንዛቤ ፈጠራ ስራ በስፋት መሰራቱንም ተናግረዋል። በዚህም ካሁን ቀደም በዘርፉ የተሰማሩትን ከማስቀጠል ባለፈ በበጀት ዓመቱ 159 ሺህ 686 አዳዲስ ዜጎችን ወደ ዘርፉ ማስገባት መቻሉን ጠቅሰዋል። በሌላ በኩል በመዲናዋ የሚገኙ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ 2 ሺህ 565 ተቋማት ወደ ግብርና ስራ እንዲገቡ መደረጉን ጠቁመዋል። ከነዚህም መካከል 1ኛ እና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፣ ጤና ጣቢያዎች እና ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንደሚገኙበት ጠቅሰው፤ ሰራተኞች ምርቶችን በተመጣጣኛ ዋጋ ገዝተው እንዲጠቀሙ እድል መፍጠሩንም ገልጸዋል። የከተማ ግብርና ልማት በገበያ የምርት እጥረት እንዳይኖር ከማድረግ ባሻገር በበጀት አመቱ ለ9 ሺህ 526 ወጣቶች የስራ እድል መፍጠሩን ጨምረው ገልፀዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር፣ በእንስሳት እርባታ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ምርት ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የመዲናዋ ነዋሪዎች የተናገሩት። በዘርፉ ከተሰማሩት መካከል ወጣት ነብዩ ማሞ በግል ተቋም ተቀጥሮ ይሰራ እንደነበረ ገለፆ፤ የከብት እርባታ ስራ ከጀመረ ወዲህ ግን ትርፋማ መሆኑን ተናግሯል። በዚህም በውስን በጎችና በአንድ ላም የጀመረው ስራ አሁን ላይ የተሻለ ውጤት እያስገኘለትና ከራሱ አልፎ ለሌሎች ወጣቶች የስራ እድል ለመፍጠር እንዳስቻለው ጠቅሷል። በወተት ላም እርባታ፣ በዶሮ እርባታና እንቁላል ምርት ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን የሚገልጹት ደግሞ አቶ ፋሲል አዘነ የተባሉ የከተማዋ ነዋሪ ናቸው። አቶ ፋሲል ከ3 አመት በፊት ስራውን ሲጀምሩ ከ6 ላሞች በቀን 125 ሊትር ወተት ለገበያ ሲያቀርቡ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ላይ ወደ 57 ላሞች በማርባት በቀን 250 ሊትር ወተት ለገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። አሁን ላይ ለበርካታ ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር መቻላቸውንም ነው የተናገሩት ።
የሀገር ውስጥ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎትን በጥራትም በስፋትም ለማሻሻል ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተከናወኑ ነው - የኢትዮጵያ አየር መንገድ
Jul 13, 2025 78
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ የሀገር ውስጥ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎትን በጥራትም በስፋትም ለማሻሻል ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ። የኮምቦልቻ ተርሚናል በተያዘው በሐምሌ ወር መጨረሻ እንደሚመረቅ ተመላክቷል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በኢትዮጵያ ትልቁን የአየር ትራንስፖርት የሚሰጠው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ብቻ መሆኑን ገልጸዋል። አሁን ላይ በ22 ከተሞች የበረራ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም በአፍሪካ ትልቅ አገልግሎት መሆኑን ጠቁመዋል። አገልግሎቱ አሁንም በቂ አለመሆኑን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈፃሚው ደረጃውን በጥራትም ሆነ በስፋት ለማሳደግ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከእነዚህም መካከል መንገደኞች የሚስተናገዱባቸው ተርሚናሎች ደረጃቸውን የጠበቁ በማድረግ ረገድ በበርካታ ኤርፖርቶች ከፍተኛ ስራ መሰራቱን አስታውቀዋል። በተጨማሪም የአዳዲስ የተርሚናሎች ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው የኮምቦልቻ ተርሚናል ግንባታ ስራም በተያዘው የሐምሌ ወር መጨረሻ እንደሚመረቅ ተናግረዋል። በተጨማሪም በሽሬ፣ ነቀምት እና ደምቢዶሎ አዳዲስ ተርሚናሎች ለመገንባት እቅድ መያዙን ጠቁመዋል። ነባር የአውሮፕላን መንደርደሪያዎችን በማደስ ትልልቅ አውሮፕላኖችን ማስተናገድ በሚችሉበት ደረጃ ከፍ የማድረግ ስራዎችም እየተሰሩ መሆኑን አመላክተዋል። ምንም ኤርፖርቶች ባልነበሩባቸው አካባቢዎችም ስድስት ኤርፖርቶች እየተገነቡ መሆናቸውንም ነው ዋና ሥራ አስፈፃሚው የገለጹት። ከእነዚህም መካከል የያቤሎ ኤርፖርት በነሐሴ ወር እንደሚመረቅ ተናግረዋል። አየር መንገዱ የሀገር ውስጥ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎትን በጥራትም ሆነ በስፋት ለማሻሻል ዘርፈ ብዙ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወጪን በራስ አቅም የመሸፈን ሂደቱን አሳድጓል
Jul 13, 2025 69
አሶሳ፤ ሐምሌ 6/2017 (ኢዜአ)፦በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በ2017 በጀት ዓመት በቅንጅት በተሰበሰበ ገቢ ወጪን በራስ የመሸፈን ሂደቱን በማሳደግ ላይ መሆኑን የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን አስታወቀ። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ተፈሪ አበበ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በበጀት ዓመቱ 4 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ዕቅድ ተይዞ ሲሰራ ቆይቷል። በበጀት ዓመቱን በተቀናጀ አኳኋን በተሰራው ሥራም ከእቅድ በላይ አምስት ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ተችሏል ብለዋል። ከተለያዩ ተቋማት ጋር የነበረው ቅንጅታዊ አሰራር መጠናከር፣ ዘመናዊ የታክስ አስተዳደር ስርዓት መስፈን እና የህግ አሰራሮች ላይ ማሻሻያ መደረጉ የላቀ አፈጻጸም እንዲመዘገብ አድርጓል ብለዋል። ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ46 በመቶ ብልጫ እንዳለው አቶ ተፈሪ አስታውቀዋል። ክልሉ የራሱን ወጪ የመሸፈን አቅሙን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው በዚህ ዓመት የራሱን ወጪ የመሸፈን አቅሙ ወደ 60 በመቶ ከፍ ማለቱን ተናግረዋል። ግብር ከፋዩ ግብርን በወቅቱ የመክፈል እና የግብርን አስፈላጊነት እየተገነዘበ በመሆኑ የታክስ ማጭበርበር እና ስወራ እየቀነሰ መምጣቱን አመላክተዋል። ክልሉ ካለው የገቢ አማራጭ አንፃር መሰብሰብ የሚገባውን ገቢ አላገኘም ያሉት አቶ ተፈሪ ተጨማሪ የገቢ አማራጮች ላይ ጥናት እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።
በዘንድሮ የመኸር ወቅት እስከ አሁን 7 ሚሊየን ሄክታር መሬት በዘር ተሸፍኗል
Jul 13, 2025 54
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦በ2017/18 የመኸር ወቅት እስከ አሁን 7 ሚሊየን ሄክታር መሬት በዘር መሸፈኑን የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ገለጹ። የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የሚያስችል ስራ እየተከናወነ ይገኛል። በግብርናው ዘርፍ በመኸር፣ በበልግ እንዲሁም በመስኖ ልማት ስራዎች ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ ሥራዎች አመርቂ ውጤቶች መመዝገቡን አስታውሰዋል። በዚህ ዓመት በመላ አገሪቱ 21 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በመኸር እርሻ በተለያዩ ሰብሎች ዘር እንደሚሸፈን ገልጸዋል። አሁን ላይ በከፍተኛ ሁኔታ የዘር ስራ የሚከናወንበት በመሆኑ እንደ በቆሎ ያሉ የአገዳ ሰብሎች ቀድሞ መዘራታቸውን ጠቁመው፣ ጤፍ፣ ስንዴ፣ ገብስና ሌሎች እንደየ አካባቢው ሥነ-ምህዳር እየተዘሩ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም እና ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ በመፍጠር ጭምር በመሰራቱ በዚህ ዓመት የተሻለ ምርት ይጠበቃል ብለዋል። ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የሚያችሉ የአፈር ማዳበሪያ፣ የምርጥ ዘር እና የተለያዩ ግብዓቶች ለአርሶ አደሩ በወቅቱ እንዲደርሱ መደረጉንም ተናግረዋል። የመኸር የእርሻ ጊዜ ለኢትዮጵያ ትልቁ የምርት ጊዜ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፤ በዓመቱ በአጠቃላይ ከሚመረተው ምርት 70 በመቶ የሚሆነው በዚሁ ወቅት የሚለማ መሆኑንም ተናግረዋል። ሚኒስትሩ እንደገለጹት ዘንድሮ 13 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በኩታ ገጠም የሚለማ ሲሆን ይህም ከባለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር እድገት ማሳየቱን ገልጸዋል። አርሶ አደሩ በኩታ ገጠም በሚሰራበት ወቅት ምርታማነቱ የበለጠ እንደሚጨምር አስታውሰው ይህም የበለጠ መጠናከር እንዳለበት አስታውቀዋል። 6 ሚሊየን ሄክታር መሬት በመካናይዜሽን የታረሰ መሆኑን ገልጸው ይህም ከባለፈው በ1 ሚሊየን ሄክታር መሬት ብልጫ እንዳለው ጠቅሰዋል። የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ትልቁ ለውጥ የአርሶ አደሮች የቴክኖሎጂን መጠቀም ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ በመምጣቱ መሆኑንም ተናግረዋል። በመኸር ወቅት 21 ሚሊየን ሄክታር መሬት በሰብል በመሸፈን ከ659 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ ይገኛል።
የገጠር ኮሪደር ልማት የኅብረተሰቡን ዘርፈ ብዙ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ትልቅ ኢኒሼቲቭ ነው
Jul 12, 2025 76
ሚዛን አማን፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የገጠር ኮሪደር ልማት የኅብረተሰቡን ዘርፈ ብዙ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ትልቅ ኢኒሼቲቭ መሆኑን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮችና ሴክተር ክትትል ሚኒስትር ዴኤታ አክሊሉ ታደሰ ገለጹ። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤትና ተጠሪ ተቋማት በቤንች ሸኮ ዞን የገጠር ኮሪደር ልማትን እሳቤ አሟልተው የሚገነቡ አምስት ሞዴል ቤቶች ግንባታ ሥራን አስጀምረዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮችና ሴክተር ክትትል ሚኒስትር ዴኤታ አክሊሉ ታደሰ እንዳሉት የገጠር ኮሪደር ልማት እሳቤ የገጠር ነዋሪዎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ትልቅ ሀገራዊ ኢኒሼቲቭ ነው። በዚህም ለአርሶ እና አርብቶ አደሩ ጤናማና ምቹ የአኗኗር ስርአት ከመፍጠር ባለፈ ከምርታማነት ጋር ለማስተሳሰር ግብ ተይዞ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የሞዴል ቤቶች ግንባታ ጽዳቱን የጠበቀ መኖሪያ ቤት ከመገንባት ጀምሮ የሌማት ትሩፋት፣ የጓሮ አትክልትና ፍራፍሬ፣ የአረንጓዴ ሥፍራና ለማኅበራዊ አገልግሎት የሚውሉ መስኮችን ያካተተ መሆኑን ጠቅሰዋል። ለዚህም የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የገጠር ኮሪደር እሳቤን ታሳቢ ያደረጉ አምስት ሞዴል ቤቶችን በጉራፈርዳ ወረዳ እንደሚገነባና ከእዚህም ሌሎች አይተው እንዲያስፋፉ የሚደረግ መሆኑን ገልጸዋል። የገጠር ኮሪደር ልማት ተግባር የገጠር ነዋሪዎች አኗኗርን ዘመናዊ በማድረግ ለብልጽግና ጉዞ ትልቅ መሠረት የሚጥል መሆኑንም ነው ሚኒስትር ዴኤታው የተናገሩት። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) በበኩላቸው መንግስት የከተማና የገጠር ነዋሪዎችን ያማከለ የልማት ኢኒሼቲቮችን በመዘርጋት ሁሉንም ተጠቃሚ ለማድረግ እየሠራ ነው ብለዋል። በክልሉ የተለያዩ ቀበሌዎች የተጀመሩ የገጠር ኮሪደር ልማት ሥራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ ገልጸው፣ ልማቱንም በምግብ ራስን ለመቻል ከሚሰራው ሥራ ጋር ማቆራኘት እንደሚገባ ገልጸዋል።
በድሬዳዋ አስተዳደር የሚሰበሰብ ገቢ መጨመር የህዝብን የልማት ጥያቄ በራስ ገቢ የመመለስ አቅምን አሳድጎታል
Jul 12, 2025 69
ድሬዳዋ፣ ሐምሌ 5/2017 (ኢዜአ)፡-በድሬዳዋ አስተዳደር የሚሰበሰበው ገቢ እየጨመረ መምጣት የህዝብን የልማት ጥያቄ በራስ ገቢ የመመለስ አቅምን ከ70 በመቶ በላይ ማድረሱን የአስተዳደሩ ገቢዎች ባለስልጣን አስታወቀ። የድሬዳዋ ገቢዎች ባለስልጣን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡም ተገልጿል። የድሬዳዋ አስተዳደር ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ አብዱልሰላም መሐመድ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የገቢ አሰባሰብና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ ላይ ዛሬ መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ዳይሬክተሩ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ አገራዊ ለውጡን ተከትሎ በድሬዳዋ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ሃብት የሚስተካከል ገቢ ለመሰብሰብ በተሰራው ሥራ አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል። ከሀገራዊ ለውጡ በፊት በአስተዳደሩ የነበረውን ዓመታዊ ገቢ 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር እንደነበር አስታውሰው፣ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ መሰረታዊ ሪፎርም በመካሄዱና ዲጂታል አሠራሮች በመዘርጋታቸው ገቢው በየዓመቱ በቢሊዮን ብሮች ጨምሯል ብለዋል። ለአብነት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከመንግስትና ከማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች 6 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ከ5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ተችሏል ብለዋል። በእዚህም የዕቅዱን 86 በመቶ ማሳካት መቻሉን ጠቅሰው የዘንድሮ ገቢ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ1 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል። በአስተዳደሩ የሚሰበሰበው ገቢ እየጨመረ መምጣት የህዝብን የልማት ጥያቄዎች በራስ ገቢ የመመለስ አቅምን በማሳደግ ከ70 በመቶ በላይ ማድረሱንም አቶ አብዱልሰላም አስታውቀዋል። ይህም ቢሆን እያደገ የመጣውን የነዋሪውን የልማት ጥያቄዎች በአግባቡ ለመመለስ ገቢን አሟጦ የመሰብሰብ ሥራ በቀጣይም ትኩረት ተሰጥቶት እንደሚከናወን አቶ አብዱልሰላም ገልጸዋል። በቀጣይም በተለይ በዘርፉ የሚስተዋሉ ብልሹ አሠራሮችን በማረም፣ ዘመናዊ የግብር አሰባሰብ ስርአትን በመተግበርና ያለ ደረሰኝ የሚፈፀም ግብይትን በመከላከል የተሻለ ገቢ ለመሰብሰብ ይሰራል ብለዋል።
በመዲናዋ ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎትን ተደራሽ የማድረግ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 12, 2025 60
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ ቀልጣፋ የፍትሕ አገልግሎትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ የማድረግ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር 4ኛ መደበኛ ጉባኤውን የተለያዩ ውሳኔዎችና ሹመቶችን በማጽደቅ ተጠናቋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአዲስ አበባ ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቶች ፕሬዝዳንት ተስፋዬ መለሰ የፍርድ ቤቶችን የ2017 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። በበጀት ዓመቱ ፍርድ ቤቶች ለሚቀርቡላቸው ጉዳዮች ቀልጣፋ፣ ውጤታማና ተደራሽ የዳኝነት አገልግሎት ለመስጠት ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል። የፍርድ ቤት የአገልግሎት ቅልጥፍና መለኪያዎች የመዛግብት ማጣራት ምጣኔና በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ውስጥ ውሳኔ መስጠት መሆኑን በሪፖርታቸው አመላክተዋል። በ2017 በጀት ዓመት የመዛግብት የማጣራት ምጣኔን 97 በመቶ ለማድረስ ታቅዶ በሁሉም ፍርድ ቤቶች መሰራቱን አብራርተዋል። ከ2016 በጀት ዓመት የዞሩና በ2017 አዲስ የተከፈቱትን ጨምሮ ከአጠቃላይ 162ሺህ 97 መዛግብት ውስጥ 159 ሺህ 65ቱ እልባት አግኝተዋል ብለዋል። ዓመታዊ የመዛግብት የማጣራት ምጣኔውም 98 በመቶ መፈጸሙን ነው ያነሱት። የዳኝነት ውጤታማነትን ለማረጋገጥ ዳኞች ስራቸውን ሲያከናውኑ ከፈጻሚው አካል፣ ከፍርድ ቤት አመራሮችና ከጎንዮሽ ተጽእኖ ነጻና ገለልተኛ ሆነው እንዲያገለግሉ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። በፍርድ ቤቶች የአገልግሎት አሰጣጥን የበለጠ ውጤታማ ለማድረግና የተገልጋይ እርካታን ለመጨመር የተለያዩ የሪፎርም ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ አብራርተዋል። የፍርድ ቤት አገልግሎትን በቴክኖሎጂ መደገፍ፣ ቀልጣፋና ተደራሽ አገልግሎት መስጠት ብልሹ ስነ-ምግባር የታየባቸው ሰራተኞችና ዳኞች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ፍርድ ቤቶችን ማጠናከር የዜጎችን መብት ለማስጠበቅና ህጎችን በትክክል በመተግበር የፍትሕ አገልግሎት ውጤታማነትን ለመጨመር ያግዛል ብለዋል። ልማትን ለማፋጠን፣ የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥና ፍትሃዊነት ለማስፈን በፍርድ ቤቶች የተጀመሩ ሪፎርሞችን ማጠናከር እንደሚገባም ነው አፅንኦት የሰጡት። ከተማ አስተዳደሩም ለፍርድ ቤቶች አስፈላጊውን መሰረተ ልማት በማሟላት ግልጽ እና ቀልጣፋ የፍትህ አገልግሎትን እውን ለማድረግ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ከንቲባዋ አረጋግጠዋል። የምክር ቤት አባላት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍርድ ቤቶች የ2017 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ላይ ያነሷቸው አስተያየቶች በግብዓትነት በመውሰድና ለጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ሪፖርቱ ጸድቋል።
በመዲናዋ በ2018 በጀት ዓመት ለሰው ተኮር እና ድህነት ቅነሳ የልማት ስራዎች ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 12, 2025 57
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በ2018 በጀት ዓመት የሰው ተኮር እና የድህነት ቅነሳ የልማት ስራዎችን ለማጠናከር ትኩረት መስጠቱን አስታወቀ። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ አብዱልቃድር ሬድዋን የከተማ አስተዳደሩን የ2018 በጀት ዓመት ዝርዝር የበጀት መግለጫ ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። የ2018 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫዎች ባለፉት ሁለት ዓመታት የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች፣ የኮሪደር ልማትና አገልግሎት አሰጣጥን ማዘመን እንደሆኑ ጠቅሰዋል። በተመሳሳይ የቤት ልማት ግንባታን የበለጠ በማጠናከር በአስር ዓመት መሪ የልማት እቅድና በሁለተኛው የአምስት ዓመት የተቀመጡ ስትራቴጂክ ግቦችን ማሳካት ማዕከል ያደረገ መሆኑን አብራርተዋል። በዚህም በ2017 የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ስራዎችን ማጠናቀቅ፣ ነባርና አዳዲስ የመኖሪያ ቤት ግንባታዎችን ማጠናቀቅ፣ የከተማዋን የቱሪስት መዳረሻነት የሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶችን ማስፋት ትኩረት ተሰጥቷቸዋል። እንደ ቢሮ ሃላፊው ገለጻ፤ ሰው ተኮርና ድህነት ቅነሳ ላይ ያተኮሩ የልማት ስራዎችን ማጠናከርና ሌሎች በበጀት ዓመቱ የትኩረት አቅጣጫዎች ናቸው። ይህንንም የልማት እቅድ ለማሳካት በ2018 በጀት ዓመት አጠቃላይ 350 ነጥብ 13 ቢሊዮን ብር በጀት መያዙን ገልጸዋል። ለ2017 በጀት ዓመት ከጸደቀው የወጪ በጀት አንጻር የዘንድሮው 108 ነጥብ 83 ቢሊዮን ብር ጭማሪ እንዳለው ተናግረዋል። ለበጀቱም ከታክስ ገቢ 238 ነጥብ 93 ቢሊዮን ብር፣ ታክስ ካልሆኑ ምንጮች 46 ቢሊዮን ብር፣ ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች 56 ነጥብ 24 ቢሊዮን ብርና ከሌሎችም ለመሰብሰብ መታቀዱን ገልጸዋል። የካፒታል በጀት የከተማ አስተዳደሩ የትኩረት አቅጣጫ ለሆኑ የቤት፣ የኮሪደር ልማትና ሌሎች ሰው ተኮር ለሆኑ ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ ለማዋል ከፍተኛውን ድርሻ ይዟል ነው ያሉት። የምክር ቤት አባላት ከተማ አስተዳደሩ አጠቃላይ ለ2018 የያዘው በጀት በከተማዋ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን በመፈጸም ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርግ እንደሆነ አንስተዋል። አባላቱ ከሥራ ዕድል ፈጠራና ከመስሪያ ቦታ ግንባታ ጋር በተገናኘ ትኩረት ማግኘት አለባቸው በሚል ላነሷቸው ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የቢሮው ሃላፊው፥ በበጀት ዓመቱ ለስራ ዕድል ፈጠራ ትልቅ ሚና ላላቸው ዘርፎች ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። ምክር ቤቱ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2018 በጀት ዓመት የቀረበውን የበጀት ውሳኔ ሃሳብ መርምሮ አጽድቋል።
ስርዓተ ምግብ ምንድን ነው?
Jul 12, 2025 47
ሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ ከሐምሌ 20 እስከ 22 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል። ዓለም አቀፍ ሁነቱን ኢትዮጵያ እና ጣልያን በጋራ ያዘጋጃሉ። የስርዓተ ምግብ ሽግግር እና ትራንስፎርሜሽን ጉባኤው የሚያጠነጥንበት አበይት አጀንዳ ነው። ለመሆኑ ስርዓተ ምግብ ሲባል ምን ማለት ነው? የሚለውን ጉዳይ እንመልከት። ስርዓተ ምግብ(Food System) የምግብ ማምረት፣ ማቀነባበር፣ ማሰራጨት፣ መጠቀም እና ማስወገድ ውስጥ ያሉ ሂደቶችና ተግባራትን አጠቃሎ የያዘ ሀሳብ ነው። ህዝብን በመመገብ ውስጥ ሚና ያላቸው ሰዎች፣ ፀጋዎች፣ ተቋማትና መሰረተ ልማቶችን ያካትታል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "ከራዕይ ወደ ተግባር፤ የኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ" በሚል መሪ ሀሳብ ዓበይት ትኩረቱን በኢትዮጵያ ሥርዓተ ምግብ ላይ ያደረገ ውይይት ሐምሌ 3 ቀን 2017 ዓ.ም አካሂዷል። የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ(ዶ/ር) በምግብ ስርዓት ሽግግር ከምርት እስከ ተጠቃሚ ባለው ሰንሰለት ውስጥ ሁሉን አቀፍ ስራ እየተከናወነ መሆኑን አንስተዋል። በስርዓተ ምግብ ሂደት ውስጥ ካሉ ጉዳዮች አንዱ እንኳን ቢጓደል ሂደቱ ምሉዕ እንደማይሆንም ገልጸዋል። ምርት እርሻ፣ የአሳ ምርት፣ የከብት እርባታ እና የተለያዩ የምግብ አመራረት አይነቶችን ያካተተ ነው። ማቀነባበር ጥሬ ምግብን ጥቅም ላይ ወደሚውሉ ምርቶች የመቀየር ሂደት ሲሆን ስርጭት ትራንስፖርት፣ የመጋዘን ክምችትና ገበያ ማድረስን በስሩ ይዟል። መጠቀም በሚባለው ደረጃ ምግብ መግዛት እና መብላት ነው። በምግብ እሴት ሰንሰለት ውስጥ የምግብ ጥራትና ብዛት ጥራት መቀነስ፣ የሚጣሉ ትራፊ ምግቦች አስተዳደርና የምግብ ተረፈ ምርቶችን ወደ ተፈጥሮ ማዳበሪያ (ኮምፖስት) መቀየር የመጨረሻው የስርዓተ ምግብ ሂደት መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ይገልጻሉ። የኢኮኖሚ ስርዓት፣ ልማዳዊ ድርጊቶች፣ የመንግስት ፖሊሲዎች፣ የከባቢ አየር ሁኔታ እንዲሁም ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን በስርዓተ ምግብ ውስጥ ያላቸው ሚና ወሳኝ ነው። ስርዓተ ምግብ ሁለንተናዊ እና ሁሉን አቀፍ መሆኑ በኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት የሽግግር ጉዞ እውን እንዲሆን ትልቅ ጠቀሜታም አለው።
ኢጋድ ለአህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ትግበራ በቁርጠኝነት መስራቱን ይቀጥላል
Jul 12, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በየነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) ለአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ተፈጻሚነት በቁርጠኝነት መስራቱን እንደሚቀጥል የተቋሙ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) ገለጹ። 47ኛው የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት እና 7ኛው የህብረቱ ቀጣናዊ ማህበረሰቦች የመንፈቅ ዓመት የጋራ የትብብር ስብሰባ በኢኳቶሪያል ጊኒ ማላቦ እየተካሄደ ይገኛል። በተጓዳኝም ሶስተኛው በአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ትግበራ ላይ ያተኮረ የቀጣናዊ ማህበረሰቦች ኃላፊዎች የጋራ ስብሰባ ተካሂዷል። ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ማህበረሰቦች የተቀናጀ የመሰረተ ልማት ትስስር፣ የንግድ ልውውጥና የፖሊሲ ተጣጣሚነትን በመፍጠር የአፍሪካን የኢኮኖሚ ትስስር እውን በማድረግ ያላቸው ቁልፍ ሚና በስብሰባው ተነስቷል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በየነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) በስብሰባው ስለ ኢጋድ ቀጣናዊ የመሰረተ ልማት ማስተር ፕላን ያነሱ ሲሆን ማዕቀፉ ከአፍሪካ ነጻ ንግድ ቀጣና እና አጀንዳ 2063 ጋር የሚመጋገብ መሆኑን ገልጸዋል። ኢጋድ ለአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ስምምነት ትግበራ በቁርጠኝነት መስራቱን አጠናክሮ እንደሚቀጥል መግለጻቸውን ኢዜአ ከተቋሙ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ለገጠር መንገድ ተደራሽነት ትኩረት ተሰጥቷል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Jul 12, 2025 66
ወላይታ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ብልጽግናን እውን ለማድረግ ለገጠር መንገድ ተደራሽነት ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ በወላይታ ዞን ዳሞት ጋሌ ወረዳ ከ36 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነባውን 20 ኪሎ ሜትር የገጠር ተደራሽ መንገድ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። በዚህ ወቅት ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት ገጠርን ከከተማ የሚያገናኝ መንገድ መገንባት አርሶ አደሩ የግብርና ምርቱን ለገበያ ለማቅረብና የፋብሪካ ሸቀጦችን በቀላሉ ወደ አካባቢው ማስግባት የሚያስችለው ነው። ይህም የአርሶ አደሩን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ያሳድጋል ያሉት አቶ ጥላሁን፣ የክልሉ መንግስት የህዝብን የመንገድ ተደራሽነት ጥያቄ ለመፍታት ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን አመልክትዋል። ዛሬ የተመረቀው መንገድ ለእዚህ አንድ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፣ ህብረተሰቡ የተገነቡ መንገዶች ለረጅም ጊዜ አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ መጠበቅ እንዳለበትም አሳስበዋል። የመንገዶቹ መገንባት የአርሶ አደሮችን ማህበራዊ ግንኙነት እንደሚያቀላጥፍ የገለጹት ደግሞ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ ናቸው። የመንገዶቹ መጠናቀቅ የግብርና ውጤቶችን በቀላሉ ወደ ከተማ ለመውሰድ እንዲሁም ነፍሰጡሮችን ጨምሮ ህሙማንን ወደ ጤና ተቋማት በፍጥነት ለማድረስ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል። የመንገዶቹ ግንባታ በታለመለት የጊዜ ገደብ ውስጥ እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላደረጉ ባለድርሻ አካላት ምስጋና አቅርበዋል። መንገዱ ከቦዲቲ ከተማ ተነስቶ ቦሎሶ ሶሬ ወረዳን በማቋረጥ ወደ ወላይታ ሶዶ ከተማ ከሚወስድ የአስፖልት መንገድ ጋር እንደሚያገናኝ ተገልጿል። በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ርዕሰ መስተደድር ጥላሁን ከበደ፣ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) እንዲሁም የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
በዞኑ ከ800 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመኸር አዝመራ እየለማ ይገኛል
Jul 12, 2025 63
አምቦ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን ከ800ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመኸር አዝመራ እየለማ መሆኑን የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በዞኑ ወልመራ ወረዳ በዘንድሮው መኸር አዝመራ በኩታ ገጠም የሚለማ ገብስ ዘር ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ተካሂዷል። የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ጽህፈት ቤት ኃላፊ ተረፈ አራርሳ እንደገለጹት በመኸር እርሻው 889ሺህ ሄክታር መሬት በዘር የመሸፈን ስራ እየተከናወነ ነው። በመኸር አዝመራው በቆሎ፣ ገብስ፣ ማሽላ እና ስንዴ በኩታ ገጠም የሚለማ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 60ሺህ 425 ሄክታር መሬት የሚሆነው በገብስ እንደሚለማ ተናግረዋል። በእስካሁኑ ሂደትም ከታረሰው መሬት ከ50 በመቶ በላይ የሚሆነው በዘር መሸፈኑን ገልጸው ከግብዓት አንጻርም ምርጥ ዘር እና የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሮች በስፋት እየቀረበ መሆኑን አብራርተዋል። በምርት ዘመኑ የተሻለ ምርት ለማግኘት 9ሺህ 146 ሄክታር በአሲድ የተጠቃ መሬት በኖራ በማከም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። የወልመራ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርናና መሬት አስተዳዳር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ደሳለኝ ተሾመ፤ የወረዳው አርሶ አደሮች የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴን እየተለማመዱ መምጣታቸውን ገልጸዋል። በዚህም ምርትና ምርታማነት እያደገ መምጣቱን ገልጸው በዘንድሮ መኸር እርሻ በወረዳው 32ሺህ 760 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት 2ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥም በወረዳው አራት ቀበሌዎች 5ሺህ 700 ሄክታር መሬት በኩታ ገጠም በቢራ ገብስ የማልማት ስራ ተጀምሯል ብለዋል። በወረዳው 9ሺህ አርሶ አደሮች በኩታ ገጠም ተደራጅተው በአሲድ የተጠቃ መሬትን በኖራ በማከም የግብርና ልማቱን ውጤታማ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የወረዳው አርሶ አደሮች በበኩላቸው ገብስን በኩታ ገጠም ማልማት እምብዛም ያልተለመደ መሆኑን ገልጸው ዘንድሮ በወረዳው ግብርና ጽህፈት ቤት በተደረገላቸው ድጋፍ ገብስን በኩታ ገጠም በማልማት ምርታቸውን ለፋብሪካ ለማቅረብ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። አርሶ አደር አሰፋ አንጋሱ፣ መሬታቻው በአሲድ የተጠቃ በመሆኑ የሚያገኙት ምርት አነስተኛ እንደነበረ በማንሳት ከግብርና ባለሙያዎች ጋር በመተባበር መሬታቸውን በኖራ በማከም ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰሩ ነው። ሌላው አርሶ አደር ሁንዴ ቶላ፤ በአሲድ የተጠቃ መሬታቸውን በኖራ አክመው የሰብል ምርታማነትን ማሳደግ ከጀመሩ ሶስት ዓመታት እንደሆናቸው አስታውሰዋል። በዚህም የመሬቱ የአፈር ለምነት ወደ ቀድሞ ሁኔታው በመመለሱ በየዓመቱ የሚያገኙት ምርት እያደገ መምጣቱን ገልጸው ዘንድሮም ከገብስ ልማት ተጠቃሚ ለመሆን መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
በከተማው የሌማት ትሩፋት አምራቹ ለሸማቹ የፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረቡ የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ እያስቻለ ነው
Jul 12, 2025 44
ባሕር ዳር፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ በባሕርዳር ከተማ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር አምራቹ ለሸማቹ የፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋና በበቂ ሁኔታ በማቅረቡ የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑ ተገለጸ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት ተጀምሮ በውጤታማነት የቀጠለው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በአጭር ጊዜ ውስጥ የዜጎችን ህይወት በመለወጥ ተጨባጥ ለውጥ እያመጣ ነው። መርሃ ግብሩ በውጤታማነት ከቀጠለባቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች መካከል በአማራ ክልል ባህርዳር ከተማ አንዱ ሲሆን፤ ጥምር ግብርናን በማለማመድ ጭምር አዲስ የስራ ባህልን ፈጥሯል። በባህርዳር ከተማ የአጼ ቴዎድሮስ ክፍለ ከተማ ነዋሪ አቶ አይሸሽም ዓለሙ፤ ባላቸው 600 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ሰው ሰራሽ የዓሳ ኩሬ በማዘጋጀት ዓሳ እያረቡ፣ አትክልትና ፍራፍሬ በማልማትና ዶሮ በማርባት ላይ እንደሚገኙ ለኢዜአ ገልጸዋል። አሁን ላይ 197 እንቁላል ጣይ ዶሮዎችና በኩሬ ዓሳ ከማርባት ባሻገር ፓፓያ፣ ሰላጣና ቆስጣን ጨምሮ ሌሎች አትክልትና ፍራፍሬ በማልማት ላይ እንደሆኑ ተናግረዋል። ከዓሳ ኩሬው የሚወጣው ውሃ ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማቱ እንደ ማዳበሪያ ያገለግላል ያሉት አቶ አይሸሽም፤ የአትክልት ተረፈ ምርቱ ደግሞ ለዓሳ፣ ለዶሮና ለራሱ አትክልቱ ማዳበሪያ ሆኖ ያገለግላል ብለዋል። ለዘመናት በዘልማድ ያካሂዱት የነበረው የግብርና ስራ ውጤታማ እንዳላደረጋቸው አውስተው፤ በሌማት ትሩፋት መሳተፍ ከጀመሩ ወዲህ በዓመት ከፍጆታቸው አልፎ ምርቶቹን ለገበያ በማቅረብ ከፍተኛ ገቢ እያገኙ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። የገነት፣ ዮሴፍና ጓደኞቻቸው የዓሳ፣ ዶሮ ርባታና አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ማህበር ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ገነት አባው በበኩላቸው፤ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር አዲስና አዋጭ የስራ ዘርፍ ነው ብለዋል። በየቀኑ 540 እንቁላል እያገኙ መሆኑን ጠቁመው፤ ከዘርፉ ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን የዶሮዎችን ቁጥር አሁን ላይ ከአንድ ሽህ 200 በላይ ማሳደግ መቻላቸውን ገልጸዋል። በተጨማሪም የዓሳ ኩሬ በማዘጋጀት ከሚያረቡት ዓሳ በግማሽ ዓመት ብቻ ከ600 ኪሎ ግራም ያላነሰ ዓሳ በማምረት አንዱን ኪሎ ግራም "ፊሊቶ" የወጣ ዓሳ በ500 ብር እየሸጡ መጠቀማቸውን አስረድተዋል። አሁን ላይ ከራሳቸው ቤተሰብ በተጨማሪ ለዘጠኝ ሰዎች የስራ እድል መፍጠራቸውን ጠቁመዋል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር እንስሳትና ዓሳ ሃብት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ውለታው አዳነ እንደገለጹት፤ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ አዋጭ የስራ ዘርፍ ነው። በዶሮ፣ በዓሳ፣ በወተት ልማት፣ በንብ እርባታና በእንስሳት ማድለብ ተግባር ለበርካታ ስራ አጥ ወገኖች የስራ እድል በመፍጠር በከተማ አስተዳደሩ በልዩ ትኩረት እየተመራ ያለ መርሃ ግብር መሆኑን ተናግረዋል። በዶሮ እርባታ ብቻ በ125 ኢንተርፕራይዞች ለተደራጁ 3ሺህ 780 ወገኖች የስራ እድል መፈጠሩን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ በቁጥር ከ62 ሚሊዮን በላይ እንቁላል በማምረት በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ ማቅረብ መቻሉን ተናግረዋል። በየቀኑ የሚመረተውን የላም ወተት ለሕብረተሰቡ ለማቅረብም የወተት ማህበራትን በማቋቋምና የመሸጫ ሱቆችን በመገንባት እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል። መርሃ ግብሩም አምራቹ ለሸማቹ የፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋና በበቂ ሁኔታ በማቅረብ የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እየበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። ህብረተሰቡ በውስን ቦታና በአነስተኛ ካፒታል በመነሳት ለትልቅ ደረጃ የሚያደርስ ዘርፍ ላይ በመሰማራት ራሱንና ቤተሰቡን ለመጥቀም በንቃት መሳተፍ እንዳለበት አመልክተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርን ጥቅምት 24/2015 ዓ.ም በአርባምንጭ ከተማ መስጀመራቸው ይታወሳል።
ባለፉት ስድስት ዓመታት የተከናወኑ ሰው ተኮር የልማት ተግባራት ውጤት እያመጡ ነው
Jul 12, 2025 58
ጉራፈርዳ፣ ሐምሌ 5/2017 (ኢዜአ)፡-ባለፉት ስድስት ዓመታት የተከናወኑ ሰው ተኮር የልማት ተግባራት ውጤት እያመጡ መሆናቸውን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮችና ሴክተር ክትትል ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አክሊሉ ታደሰ ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤትና በተጠሪ ተቋማት በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በ35 ሚሊዮን ብር ወጪ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ቤንች ሸኮ ዞን ጉራፈርዳ ወረዳ ለሚገነቡ መኖሪያ ቤቶችና ሞዴል ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ፕሮጀክቶች የመሰረት ድንጋይ ተቀምጧል። ለፕሮጀክቶቹ የመሰረት ድንጋይ ሲቀመጥ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የካቢኔ ጉዳዮችና ሴክተር ክትትል ሚኒስትር ዴኤታ አቶ አክሊሉ ታደሰ እንደገለጹት፣ ባለፉት ስድስት ዓመታት የተከናወኑ ሰው ተኮር የልማት ተግባራት ውጤት እያመጡ ነው። በእነዚህ ዓመታት በሕዝብና በመንግስት ትብብር በየዓመቱ በሺዎች ለሚቆጠሩ አቅመ ደካሞች መኖሪያ ቤቶች ገንብቶና አድሶ ለማስረከብ መቻሉን ተናግረዋል። በእዚህም በርካቶች ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት አቶ አክሊሉ፣ በልማት ተግባሩ ከፌዴራል እስከ ክልልና ቀበሌ ድረስ ያሉ ተቋማት ተሳትፎና እገዛ እያደረጉ መሆናቸውንም ተናግረዋል። በተያዘው የክረምት ወራትም ልማቱን በማስቀጠል የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤትና ተጠሪ ተቋማት በ33 ሚሊዮን ብር አምስት የገጠር ቤቶችና አንድ ሞዴል ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት በጉራፈርዳ ወረዳ እንደሚገነቡ ገልጸዋል። የሚገነቡት የልማት ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያን ከፍታ ለማረጋገጥ የድርሻውን የሚወጣ ትውልድ ለመፍጠር ሚና እንዳለውም ጠቅሰዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በበኩላቸው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባር የእርስ በርስ መተጋገዝና መደጋገፍ ባህልን እያዳበረ መጥቷል ብለዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ ሰው ተኮር የልማት ሥራዎች ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውን ተናግረው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤትና ተጠሪ ተቋማቱ ይህን የልማት ስራ ለማጠናከር በመምጣታቸው አመስግነዋል። በክልሉ የማኅበረሰቡን የኢኮኖሚ አቅም የሚያሳድጉና የምግብ ዋስት የሚያረጋግጡ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ሲሉም ገልጸዋል። የቤንች ሸኮ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን በዘንድሮ የክረምት በጎፈቃድ አገልግሎት ሥራዎች ከ200 በላይ የአቅመ ደካማ መኖሪያ ቤቶች እድሳትና ግንባታ ሥራ እንደሚከናወን ገልጸዋል። የትውልድ ለትምህርት ንቅናቄን በስኬት አጠናክሮ ለማስቀጠል እንደሚሰራ ጠቁመው፣ ግንባታቸው እየተከናወኑ ያሉ ሰባት ሞዴል ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤቶችን በክረምቱ መጨረሻ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤትና ተጠሪ ተቋማት ተወካዮች በጉራፈርዳ ወረዳ በነበራቸው ቆይታ ችግኝ በመትከልም አረንጓዴ አሻራቸውን አሳርፈዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በፈጠረው ሀይቅ ዓሳን በማምረት ተጠቃሚ ሆነናል - የግድቡ አካባቢ ነዋሪዎች
Jul 12, 2025 59
አሶሳ፤ ሐምሌ 5/2017 (ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከፈጠረው ሀይቅ ዓሳ በማምረት ተጠቃሚ መሆናቸውን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የግድቡ አካባቢ ነዋሪዎች ገለጹ። በኢትዮጵያውያን የጋራ ትብብር የተገነባው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በ2018 ዓ.ም እንደሚመረቅ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት መግለጻቸው ይታወሳል። ግድቡ የኤሌክትሪክ ኃይል ለማመንጨት ከሚሰጠው ጥቅም ባሻገር ከግድቡ ሀይቅ የአካባቢው ነዋሪዎች ዓሳ እያመረቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። የታላቁ የህዳሴ ግድብ ከፈጠረው ሀይቅ ዓሳን ከሚያመርቱ የሸርቆሌ እና ሰዳል ወረዳ ነዋሪዎች ጋር ኢዜአ ቆይታ ያደረገ ሲሆን፤ ነዋሪዎቹም ግድቡ በፈጠረው ሀይቅ ዓሳ እያመረቱ መሆኑን ገልጸዋል። በዓሳ ምርቱ ከተሰማሩ የሸርቆሌ ወረዳ ነዋሪዎች መካከል አቶ አጅብ ሙሀመድ በህዳሴው ግድብ አማካኝነት ከተፈጠረው ሀይቅ ከሚያሰግሩት ዓሳ ቤተሰባቸውን እያስተዳደሩ ይገኛሉ። የዓሳ ምርቱን ለገበያ እያቀረቡ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ከመሆናቸው ባለፈ ለምግብነት እየተጠቀሙ መሆኑንም ተናግረዋል። የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አቶ ዘካሪያ አጀሊ በበኩላቸው፤ በማህበር ተደራጅተው ዓሳን በማምረት የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። ምርታቸውንም ለአሶሳና ለሌሎች አካባቢዎች በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው ማደጉን ገልጸው በቀጣይ የተሻለ ተጠቃሚ ለመሆን እንደሚሰሩ ገልጸዋል። ሌላው ዓሳን አዘጋጅቶ ለገበያ እያቀረበ የሚገኘው ኤሊያስ እና ጓደኞቹ ዓሳ አምራች ማህበር አባል ወጣት ደባሽ ትዜ፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ከፈጠረው ሀይቅ ላይ የዓሳ ምርት በስፋት እያገኙ መሆኑን ተናግሯል። በዓሳ ምርቱ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆኑን ጠቁሞ ማህበሩ 40 ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠሩን ገልጿል። የሚያመርቱትን ዓሳ እስከ አዲስ አበባ ድረስ በራሳቸው ተሽከርካሪ በማጓጓዝ እየሸጡ መሆኑንም ጠቅሷል። በቀን እስከ 20ሺህ ብር ገቢ እያገኙ መሆናቸውንና የኢኮኖሚ አቅማቸውን እያሳደጉ እንደሆነ የተናገሩት ደግሞ በሰዳል ወረዳ በዓሳ ምርት ላይ የተሰማሩት አቶ ነጅብ መኪና ናቸው። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርና ቢሮ የእንስሳት እና ዓሳ ግብዓት አቅርቦት ባለሙያ አቶ ገመቹ አየለ፣ በ2017 በጀት ዓመት ከታላቁ ህዳሴ ግድብ 5ሺህ 895 ቶን የዓሳ ምርት መገኘቱን ተናግረዋል። በህዳሴ ግድብ አካባቢ የሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎችም በዓሳ ምርት ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። ቢሮው ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር በማህበር ለተደራጁ ወጣቶች ጀልባ እና የዓሳ ማጥመጃ መረብ ድጋፍ ማድረጉንም ጠቅሰዋል። የሚመረተው ዓሳ ወደ ማዕከላዊ ገበያ እንዲቀርብ ለማድረግ ትልልቅ ድርጅቶች ጥያቄ እያቀረቡ መሆናቸውንም ባለሙያው አክለዋል።
የመዲናዋ የ2018 በጀት 350 ነጥብ 13 ቢሊዮን ብር ሆኖ ጸደቀ
Jul 12, 2025 69
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት የመዲናዋን የ2018 በጀት 350 ነጥብ 13 ቢሊዮን ብር አድርጎ አጸደቀ፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ስብሰባ አካሂዷል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ አብዱልቃድር ሬድዋን፥ የከተማ አስተዳደሩን የ2018 በጀት ዓመት ዝርዝር ረቂቅ በጀት ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። ለ2018 በጀት ዓመት 350 ነጥብ 13 ቢሊዮን ብር በጀት መያዙን ገልጸው፥ በጀቱ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ108 ቢሊየን ብር ወይም የ45 በመቶ እድገት እንዳለው ገልጸዋል። ከአጠቃላዩ በጀት ለመደበኛ ወጪ 91 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር፣ ለካፒታል ሥራዎች 246 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር የተመደበ ሲሆን ቀሪው 12 ቢሊዮን ብር ለመጠባበቂያ መሆኑን አብራርተዋል። የካፒታል በጀት ከፍ እንዲል የተደረገው ለሰው ተኮር ሥራዎች፣ ለቤት ልማት፣ ለኮሪደር ልማት እና ለከተማ አስተዳደሩ ወሳኝ ፕሮጀክቶች ትኩረት መስጠት በማስፈለጉ መሆኑን አንስተዋል። በጀቱ የከተማዋን ራዕይ፣ በሒደት ላይ ያሉ ፕሮጀክቶችንና አዳዲስ የልማት ፍላጎቶችን፣ የታቀዱ አስተዳደራዊ ማሻሻያዎችን፣ አገልግሎት የማዘመን ስራን በፍጥነትና በውጤታማነት ለመተግበር ታሳቢ በማድረግ መዘጋጀቱን አስረድተዋል፡፡ ከአጠቃላይ በጀቱ ከ238 ቢሊየን ብር በላይ የሚሆነው ከታክስ፣ ከማዘጋጃ ቤታዊ ገቢ ከ56 ቢሊየን ብር በላይ፣ ታክስ ካልሆነ ገቢ ከ46 ቢሊየን ብር በላይ፣ ከመንገድ ፈንድ 1.8 ቢሊየን፣ ከውጭ ብድርና እርዳታ 6 ነጥብ 98 ቢሊየን ብር እንደሚሰበሰብ ጠቅሰዋል። የምክር ቤቱ አባላትም በረቂቅ በጀቱ ላይ በመወያየት በሙሉ ድምጽ አጽድቀውታል።