ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ ከተሞች የመሬት ይዞታ ካዳስተር ምዝገባ ሥርዓት የገቢ አቅማቸውን በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው
May 29, 2026 523
አዲስ አበባ፤ግንቦት 21/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ከተሞች የመሬት ይዞታ ካዳስተር ምዝገባ ሥርዓት የከተሞችን የገቢ አቅም በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ፈንታ ደጀን ገለጹ። ከተሞች የገቢ አቅማቸውን በመጠቀም ብድር ማግኘት የሚችሉበትን ሥርዓት ለመዘርጋት እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ለኢዜአ እንዳሉት፤ ከተሞች ለአጠቃላይ ሀገራዊ ምርት ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው ናቸው። የኢትዮጵያ ከተሞች እስከ 58 በመቶ ለአጠቃላይ ሀገራዊ የምርት ድርሻ እያበረከቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ በኮሪደር፣ወንዝ ዳርቻና ዲጂታላይዜሽን የተከናወኑ ስኬታማ የልማት ተግባራት ስሉጥ ከተሞችን በመፍጠር ከፍተኛ ጠቀሜታ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊ የከተሜነት ምኅዳር የመፍጠር ሥራም ዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ የመንግሥት አገልግሎት የሚያገኙበት አስቻይ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን አንሰተዋል። የከተሞች ማዘጋጃ ቤታዊና የተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ ወደ ዲጂታል ሥርዓት መሸጋገሩም ፈጣንና ቀልጣፋ ምኅዳር መፍጠሩን አስረድተዋል። በተለይም በአንድ ማዕከል አገልግሎት ዜጎች የመንግሥት አገልግሎቶችን በተማከለ ሥርዓት በጥራትና ፍጥነት የሚያገኙበት ዕድል እንደፈጠረ ተናግረዋል። የከተሞችን የመሬት ይዞታ በፍትሐዊነት ለማስተዳደርም ምዝገባ እየተካሄደ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ 6 ነጥብ 6 ሚሊየን ፐርስል የከተማ መሬት ውስጥ 33 በመቶው ባለፉት ሶስት ዓመታት መመዝገቡን ጠቅሰው፤ በካዳስተር ስርዓት መሬትን የማስተዳደር ስራ በስፋት እየተሰራ ነው ብለዋል። ለአብነትም የአዳማ ከተማን ጨምሮ ሌሎች ከተሞች የመሬት ምዝገባ ማጠናቀቃቸው አብራርተዋል። የከተሞችን ሃብትና ገቢ የማመንጨት አቅም ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራትም ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ እንደሚገኙ አብራርተዋል። በዚህም አሁን ላይ የከተሞች ገቢ ከአራት ዓመታት በፊት ከነበረበት 10 ቢሊዮን ብር ወደ 80 ቢሊየን ብር ማድረስ እንደተቻለ ገልጸዋል። ይህም የከተሞችን ገቢ የመሰብሰብ አቅም በማሳደግ በሚያመነጩት ገቢ መጠን በመጠቀም ብድር የሚያገኙበት ሥርዓት እየተዘረጋ መሆኑን ተናግረዋል።
የአቮካዶን ምርታማነት በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታ ለማሻሻል እየተሰራ ነው
May 29, 2026 484
አዲስ አበባ፤ግንቦት 21/2018(ኢዜአ)፦ የአቮካዶን ምርታማነት በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታ ለማሻሻል እየተሰራ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ደሳለኝ ተሻለ ገለጹ፡፡ በግብርና ሚኒስቴር አዘጋጅነት በብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ዙሪያ የዘርፉን ባለድርሻ አካላት ያሳተፈ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ደሳለኝ ተሻለ እንዳሉት፤ የአቮካዶ ምርት በአገር ደረጃ ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው የግብርና ምርት ኢኒሼቲቮች ውስጥ አንዱ ሲሆን፣ ምርትና ምርታማነቱን በማሳደግ ረገድ ሰፊ ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። ይህ ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም በአገሪቱ እያደገ የመጣውን የፍራፍሬ ፍላጎት ለማሟላትና የኢትዮጵያን የኤክስፖርት አቅምን ለማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ጠቁመዋል። የአቮካዶ ምርት ለተመጣጠነ ምግብ አቅርቦት፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ እንዲሁም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎች እንዳሉትም አብራርተዋል። ሚኒስቴሩ አገር አቀፍ የአቮካዶ ልማትን ይበልጥ ለማስፋፋት፣ ምርታማነትን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገርና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ የዘርፉን ተዋናዮች፣ አምራቾችና ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ መልኩ በቅንጅት እየሠራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም መሠረት ከፍተኛ ምርት የሚሰጡና የተለያዩ በሽታዎችን የሚቋቋሙ ተመራጭ የአቮካዶ ዝርያዎች ለአርሶ አደሮች ተሰራጭተው ከፍተኛ ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። አነስተኛ አምራች አርሶ አደሮችን በክላስተር በማደራጀት፣ ዘመናዊ የኩሬ አጠቃቀምና የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂ ስልጠናዎችን በመስጠት የምርት ጥራትን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ማድረግ የሚያስችል አሠራር እየተዘረጋ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህም አርሶ አደሩን በቀጥታ ከዓለም አቀፍ ገበያ ጋር ለማስተሳሰር ትልቅ ሚና ይጫወታል ብለዋል። ይህ ብሔራዊ ፕሮግራም የአርሶ አደሩን የኑሮ ዘይቤና ገቢ ከመቀየር ባለፈ፣ በግብርናው ዘርፍ የሚገኘውን የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ገቢ በከፍተኛ መጠን ለማሳደግ የተቀረጸ ስትራቴጂካዊ እርምጃ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
በደቡብ ኦሞ ዞን በዘንድሮው የበልግ እርሻ ለገበያ ተኮር ሰብሎች ትኩረት ተሰጥቷል
May 29, 2026 281
ጂንካ፤ግንቦት 21/2018(ኢዜአ):- በደቡብ ኦሞ ዞን በዘንድሮ የበልግ እርሻ ለገበያ ተኮር ሰብሎች ትኩረት በመስጠት መሰራቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ በዞኑ በዘንድሮ የበልግ እርሻ 108 ሺህ ሄክታር መሬት መልማቱን ገልጸዋል።   አጠቃላይ ከለማው መሬት ወደ 4 ሚሊዮን የሚጠጋ ምርት ለማግኘት እንደታቀደም ጠቅሰዋል። በዘንድሮ የበልግ እርሻ ለገበያ ተኮር እና የኢንዱስትሪ ግብዓት ለሚሆኑ ስንዴ፣ ሰሊጥ፣ ካሳቫ እና ማሾ ሰብሎች ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። ቀደም ሲል አርሶና አርብቶ አደሩ ውስን ሰብሎችን ብቻ በማልማት ለገበያ የሚያቀርብበትን ሁኔታ በመቀየር ገበያ ተኮር የሆነ አመራረት በመከተል በኩታ ገጠም በስፋት የሚያለሙበት ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። ከዚህም ባሻገር አርሶና አርብቶ አደሩ በአካባቢው ያልተለመዱ እንደ ሩዝ እና ካሳቫ ምርቶችን ማምረት መጀመራቸውን አንስተው፥ በዚህም የገቢ አቅማቸው እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል።   በዞኑ ሳላማጎ ወረዳ ገሮ ቀበሌ በካሳቫ ምርት የተሰማሩት አርሶ አደር አለሙ ላስታ፥ በዘንድሮ የበልግ አዝመራ 17 ሄክታር መሬት ላይ ካሳቫ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል ። መንግስት የእርሻ መሬት እና የእርሻ ትራክተር በማቅረብ እገዛ እያደረገላቸው መሆኑን ገልፀው፥ የግብርና ባለሙያዎችም ገበያ ተኮር የሆኑ ሰብሎችን እንዲያለሙ ሙያዊ ድጋፍ እያደረጉላቸው መሆኑን ገልጸዋል። ካሳቫ በአንድ ሄክታር እስከ 300 ኩንታል ምርት የሚያስገኝ እና ቶሎ የሚደርስ ሰብል መሆኑ ደግሞ ይበልጥ ተመራጭ አድርጎታል ነው ያሉት አርሶ አደሩ።   ሌላው የወረዳው አርሶ አደር አድማሱ ጩሉ፥ በዘንድሮ የበልግ አዝመራ በኩታ ገጠም 8 ሄክታር መሬት ላይ ሩዝ እያለሙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሩዝ ውሃ በሚተኛባቸው ረግረጋማ ቦታዎች ምርት የሚሰጥ በመሆኑ ሩዝ እያለሙ መሆኑን ገልጸዋል። በአካባቢው ቀደም ሲል በቆሎ እና ማሽላ በስፋት የማልማት ልምድ እንደነበር ጠቁመው፥ አሁን ላይ በመንግሥት ድጋፍ ገበያ ተኮር የሆኑ ሰብሎችን በማልማት የተሻለ ገቢ ማግኘት መጀመራቸውን ገልጸዋል።
የመስኖ ግድቦች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገውን ጉዞ እያፋጠኑ ነው
May 28, 2026 787
ነገሌ ቦረና፣ግንቦት 20/2018 (ኢዜአ)፦በምሥራቅ ቦረና ዞን አነስተኛና መካከለኛ የመስኖ ግድቦች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገውን ጉዞ እያፋጠኑ መሆኑን የዞኑ መስኖና አርብቶ አደር ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የምሥራቅ ቦረና ዞን አብዛኛው ነዋሪ ሕይወትና መተዳደሪያው አርብቶ አደርነትና ከአነስተኛ የእርሻ ሥራ ጋር የተያያዘ ነው። አካባቢው በተደጋጋሚ ጊዜ በሚከሰት ድርቅና በተለዋዋጭ የአየር ንብረት መዛባት ምክንያት ከፍተኛ የሆነ የውኃ እጥረት ሲያጋጥመው ቆይቷል። ይህንን ለመፍታት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ትኩረት የተሰጠው አነስተኛና መካከለኛ የመስኖ መሠረተ ልማቶችን ማስፋፋት ላይ ነው። የመስኖ ግድቦቹ መገንባት ማኅበረሰቡ መደበኛውን የዝናብ ወቅትን ብቻ ከመጠበቅ ወጥቶ፣ ያለውን የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር ውኃ በአግባቡ በመጠቀም በዓመት ሁለትና ሦስት ጊዜ እንዲያመርት ዕድል ፈጥሯል። የዞኑ መስኖና አርብቶ አደር ጽሕፈት ቤት እንዳስታወቀው፤በዞኑ ቆላማ ወረዳዎች የተገነቡ ሁለት የመስኖ መሠረተ ልማቶች እየሰጡ ባለው አገልግሎት ዘርፈ ብዙ ጥቅም እያስገኙ ነው። በጽሕፈት ቤቱ የዲዛይንና ቁጥጥር ቡድን መሪ ኢንጂነር ተስፋሁነኝ ዳንኤል እንደገለጹት፤ ፕሮጀክቶቹ በተለይም ከተረጂነት ወደ ምርታማነት በሚደረገው ሽግግር ውስጥ ትልቅ እገዛ እያደረጉ ነው። በተለይም በዞኑ በሊበንና በጎሮዶላ ወረዳዎች የተገነቡት ግድቦቹ ነዋሪውን ወደ መስኖ ልማት ማስገባት ያስቻሉ ሲሆን ለምርታማነት ዕድገትም አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው ብለዋል። እነዚህ የመስኖ ፕሮጀክቶች ከ8 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የዝናብ ውኃ የማጠራቀም አቅም እንዳላቸውም ገልጸዋል። የመስኖ ፕሮጀክቶቹ ከ465 ሄክታር በላይ መሬትን በዘመናዊ መስኖ ከማልማት ጎን ለጎን፣ የአካባቢውን የመኖና የውኃ ችግር የሚያቃልሉ መሆናቸውንም አስረድተዋል። በተጨማሪም ግድቦቹ ለአሳ ሀብት ልማትና ለቱሪዝም መዳረሻነት አገልግሎት እንዲሰጡ ተደርገው የተገነቡ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ለአብነትም በዞኑ ድቤ አዳማ መስኖ ፕሮጀክት ግድብ ውስጥ እስካሁን ከ10 ሺህ በላይ የአሳ ጫጩቶች መለቀቃቸውን ገልጸዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የዞኑ ነዋሪዎች እንዳሉት፥የመስኖ ፕሮጀክቶቹ በዘመናዊ መስኖ ልማት የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥ ያግዛቸዋል። በዞኑ ሊበን ወረዳ የሲሚንቆ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ቃሲም ገመዳ እንደገለጹት፤ አካባቢው በድርቅና በዝናብ እጥረት ሳቢያ በተደጋጋሚ የመኖና የውኃ ችግር ያጋጥመው ነበር። ቀደም ሲል መኖና ውኃ ፍለጋ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ለከፍተኛ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ሲጋለጡ መቆየታቸውንም ያስታውሳሉ። በአካባቢያቸው በተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት የበጋ ስንዴን በዘመናዊ መስኖ በማልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዲሁም የእንስሳት መኖና የውኃ ችግርን ለማቃለል እንደሚያግዝ ጠቁመው፥የበጋ ስንዴ፣ ቲማቲም፣ድንችና ሽንኩርት በመስኖ ለማልማት ተዘጋጅተዋል። ሌላው ነዋሪ አቶ ጉዮ ጃተኒ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል መደበኛ ሥራቸውን ትተው የእንስሳት መኖና የመጠጥ ውኃ ፍለጋ ሩቅ መንገድ ይጓዙ እንደነበር ያስታውሳሉ። በአካባቢያቸው የተገነቡት የመስኖ ፕሮጀክቶች ከአካባቢያቸው ሳይርቁ የበጋ ስንዴ በማምረት ችግሩን በዘላቂነት ለመቋቋም እንዳስቻላቸው ገልጸዋል።
በጂማ ከተማ የሥራ ዕድል የተመቻቸላቸው ወጣቶች ተጠቃሚነታቸው አድጓል
May 28, 2026 353
ጂማ፣ ግንቦት 20/2018 (ኢዜአ)፦ በጂማ ከተማ በተለያዩ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ወጣቶች ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ገለጹ። በከተማዋ የወጣቶችን የሥራ ዕድል ለማስፋት የግብርና፣ የቴክኖሎጂና የንግድ ሥልጠናዎችን በመስጠት፣ የመሥሪያና መሸጫ ቦታዎችን በማቅረብ እንዲሁም የገበያ ትስስር በመፍጠር ረገድ ተስፋ ሰጪ ውጤቶች እየተመዘገቡ ይገኛሉ። በከተማዋ ኢዜአ ያነጋገረው ወጣት አብዱረሂም ናስር እንደገለጸው፤ የከተማ አስተዳደሩ ባመቻቸለት የሥራ ዕድል በመጠቀም የዳቦ መጋገሪያ ማሽኖችን በጥራት አምርቶ ለገበያ እያቀረበ ይገኛል። እነዚህ ማሽኖች ከውጭ የሚገቡ የዳቦ መጋገሪያ ምርቶችን በመተካት የውጭ ምንዛሬን ከማዳናቸው ባለፈ፣ ኃይል ቆጣቢ በመሆናቸው በገበያ ላይ ተመራጭ መሆናቸውን አስረድቷል። ይህም ገቢውን ከመጨመር ባለፈ ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል እንዲፈጥር እንዳገዘው ጠቁሟል።   በተመሳሳይ ዘመናዊ ቦርሳዎችንና የቆዳ ውጤቶችን በማምረት ለገበያ እያቀረቡ ከሚገኙ ወጣቶች መካከል ደርሶልኝ ሽመልስ እና ሀብታሙ ጋዲሳ ይጠቀሳሉ። ወጣቶቹ እንደሚያስረዱት፤ የሚያመርቷቸው የቆዳ ውጤቶች በቅርጽም ሆነ በጥራት የሸማቹን ፍላጎት ያሟሉ በመሆናቸው በገበያ ላይ ተወዳዳሪ መሆን ችለዋል። ሥራቸውን ይበልጥ ለማስፋፋትም የከተማ አስተዳደሩ የብድርና የመሥሪያ ቦታ እንዳመቻቸላቸው ገልጸዋል። የጂማ ከተማ የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት መምሪያ ኃላፊ አቶ አብዱልሀሚድ ኑረዲን በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በከተማዋ ለወጣቶች የሥራ ዕድልን ለማስፋፋት በርካታ የመሥሪያና የመሸጫ ሼዶች ተገንብተዋል።   በዚህም በበጀት ዓመቱ ከ3 ሺህ በላይ በማኅበራት ለታቀፉ 20 ሺህ 160 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ፣ ዕቅዱን በማሳለጥ 28 ሺህ 500 ወጣቶችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል። የወጣቶቹን ስኬት ይበልጥ ለማገዝ የሥልጠናና የብድር አቅርቦት መመቻቸቱን የገለጹት ኃላፊው፤ በበጀት ዓመቱ እስካሁን 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር የብድር አገልግሎት መቅረቡን ጠቁመዋል። ለወጣቶቹ የሥራ ዕድልን ለማስፋፋትም ለቡና መፈልፈያ፣ ለዳቦና እንጀራ መጋገሪያ፣ ለቆዳና እንጨት ሥራዎች እንዲሁም ለሌሎችም ተኪ ምርቶች ማምረቻ የሚሆኑ ሼዶች መሰጠታቸውን አክለዋል። ወደ ሥራ የገቡት ወጣቶች ምርቶቻቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ ለሕብረተሰቡ ከማቅረብ ባለፈ፣ ተኪ ምርቶችን በማምረት የሀገርን የውጭ ምንዛሬ ማዳን መቻላቸውንም አቶ አብዱልሀሚድ ገልጸዋል።  
በአማራ ክልል በዘንድሮው መኸር እርሻ ከ876 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት በሰሊጥና አኩሪ አተር ይለማል
May 28, 2026 308
ባህርዳር ፤ ግንቦት 20/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በዘንድሮው መኸር እርሻ ከ876ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ለኢንዱስትሪና ለውጭ ገበያ የሚውል የሰሊጥና የአኩሪ አተር እንደሚለማ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ሰሊጥ ከቡና ቀጥሎ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ከሚያስገኙ የግብርና ምርቶች መካከል ተጠቃሽ ነው። አኩሪ አተርም ለምግብ ዘይት ፋብሪካዎችና ለእንስሳት መኖ ኢንዱስትሪዎች ወሳኝ ግብዓት ከመሆኑም በላይ፣ በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ያለው ተፈላጊነት እየጨመረ የመጣ ሰብል ነው። ‎ ‎በአማራ ክልል ግብርና ቢሮ የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማንደፍሮ አስላከ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለፁት ለኢንዱስትሪና ለወጪ ምርት ግብዓት የሚውሉ ሰብሎችን በጥራትና በብዛት ለማምረት ግብ ተይዞ እየተሰራ ነው። ‎ ‎በዚህም በዘንድሮው የመኸር እርሻ የአየር ንበረታቸውና ስነ ምህዳራቸው ተስማሚ በሆኑ አካባቢዎች የሰሊጥና አኩሪ አተር ሰብሎች በስፋት ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ብለዋል። በዚህም በክልሉ ከሚለማው 876ሺህ 870 ሄክታር መሬት፤ 463ሺህ 566 ሄክታር በሰሊጥ ቀሪው ደግሞ በአኩሪ አተር እንደሚለማ ተናግረዋል። ‌‎ከልማቱ ከ15 ነጥብ 3 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ጠቁመው የዘር ወቅት በመድረሱም ዘርና ማዳበሪያ እየቀረበ ነው ብለዋል።
ባሕር ዳር ለነዋሪዎቿ ምቹ ለዓለምአቀፍ ጎብኚዎች ደግሞ ተመራጭ የቱሪስት ከተማ እየሆነች ነው - ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው
May 27, 2026 1012
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ ባሕር ዳር በኮሪደር ልማት ለነዋሪዎቿ ምቹ ለዓለምአቀፍ ጎብኚዎች ደግሞ ተመራጭ የቱሪስት ከተማ እየሆነች ነው ሲሉ የባህርዳር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ። የባሕር ዳር ከተማን ውበትና ፅዳት በመጠበቅ ለነዋሪዎች ምቹ፣ ለዓለም አቀፍ ጎብኚዎች ደግሞ ተመራጭና ረጅም ጊዜ የሚቆዩባት የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ የተቀረጸው ዕቅድ በተግባር እየተተረጎመ ይገኛል። ​የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው እንደገለጹት፣ ይህንን ግብ ለማሳካት የተቋቋመው የስማርት ባህርዳር ፕሮጀክት ፅህፈት ቤት መሪነቱን በመውሰድ የኮሪደርና የጣና ዳርቻ ልማቶችን ሌሊትና ቀን በከፍተኛ ፍጥነት እያከናወነ ነው።   ​የከተማዋን ገጽታ የቀየሩ የጣና እና የዓባይ ዳርቻ ፕሮጀክቶች ​የከተማዋ ተፈጥሯዊ ሀብቶች የሆኑትን የጣና ሐይቅንና የዓባይ ወንዝን ለቱሪዝም ምቹ የማድረግ ሥራ ትኩረት ተሰጥቶታል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅት በሐይቁ ዳርቻ ላይ ዘጠኝ የሚደርሱ ቦታዎች መልማታቸውን ጨምረው አስታውቀዋል። ይህም ከተማዋ፣ ነዋሪዎችና ጎብኚዎች ከሐይቁ ጋር ያላቸውን መስተጋብር በእጅጉ አሳድጎታል ብለዋል። ከዚሁ ልማት ጋር ተያይዞም የዘንባባ ፓርክ ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑ የከተማዋን ውበት ይበልጥ እንዳደመቀው ገልጸዋል። ​የኮሪደር ልማቱ ​የከተማዋን ዋና ዋና መስመሮች እያደሰ ያለው የኮሪደር ልማት ከደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተነስቶ እስከ ዓባይ ማዶ ባለው ዋና መንገድ ላይ በከፍተኛ ፍጥነት እየተገነባ ይገኛል ብለዋል።   ይህ መሠረተ ልማት ከ5 እስከ 7 ሜትር የሚደርስ ሰፊ የእግረኛ መንገድ፣ እስከ 4 ሜትር ስፋት ያላቸው ውብ አረንጓዴ መናፈሻዎች፣ ​እስከ 3 ሜትር ስፋት ያለው የተለየ የብስክሌት መንገድ፣ የስፖርት ማዘውተሪያዎች፣ የሕዝብ ማረፊያዎችና የሕፃናት መጫወቻዎች ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። ​በተጨማሪም ከቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን እስከ ፓፒረስ ሆቴል ድረስ ያለው የእግረኛ መንገድ ግንባታ እየተፋጠነ እንደሚገኝም አንስተዋል። በከተማዋ የዓባይ ወንዝን ዳርቻን ለማልማት መታቀዱንም ነው የጠቆሙት። ​የከተማዋ የኮሪደር ልማት ዕቅድ ሲቀረጽ ጀምሮ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህን ጨምሮ የፌደራል መንግሥቱ ፕሮጀክቱን በመገምገምና አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ የላቀ የመሪነት ሚና መጫወታቸውንም አስረድተዋል። ​ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በከተማዋ ተገኝተው የልማት ሥራዎቹን መገምገማቸውንና ለቀጣይ ተግባራት አቅጣጫ ማስቀመጣቸውንም ነው ያነሱት አቶ ጎሹ እንዳላማው።   ለኮሪደር ልማቱ ስኬት የከተማዋ ነዋሪዎችና ባለሀብቶች በገንዘብና በሐሳብ እያደረጉት ያለው ተሳትፎ አይተኬ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። ከተማ አስተዳደሩ ሕዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ መሰል የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው አረጋግጠዋል።
መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 356
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ ‎የሕዝብ ጤናን እየጠበቅን፣ የነዋሪዎችን መተዳደሪያ አቅም እያጠናከርን መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ግዙፉ የቦረና የመጠጥ ውኃ አቅርቦትፕሮጀክት ለኅብረተሰቡ አስተማማኝ የንጹሕ ውኃ አቅርቦት ተደራሽ በማድረግ፣ በምሥራቅ ቦረና እና በቦረና ዞኖች የሚገኙ ነዋሪዎችን ሕይወት እየቀየረ ይገኛል ብለዋል። በብዙ ኪሎ ሜትሮች የሚቆጠሩ የቧንቧ መስመሮችን፣ ዘመናዊ የውኃ ማከፋፈያ ጣቢያዎችን እና ሰፋፊ የውኃ ማጠራቀሚያዎችን ያካተተ ዘላቂ መሠረተ ልማት እየገነባን ሲሆን ይህም ድርቅን ከመመከት የላቀ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። ‎ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት ‎የሕዝብ ጤናን እየጠበቅን፣ የነዋሪዎችን መተዳደሪያ አቅም እያጠናከርን መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን ብለዋል።
በአዳማ ከተማ በተለያዩ ዘርፎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነዋሪዎች ውጤታማ በመሆናቸው ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል ፈጥረዋል
May 27, 2026 293
አዳማ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ በአዳማ ከተማ በተለያዩ ዘርፎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነዋሪዎች ውጤታማ በመሆናቸው ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ገለጹ።   ከተጠቃሚዎቹ መካከል አቶ ጌቱ ተስፋዬ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ከተማ አስተዳደሩ በቤተሰብ ብልጽግና ተደራጅተው ራሳቸውንና ማኅበረሰቡን ተጠቃሚ እንዲያደርጉ ከፍተኛ ድጋፍ እንዳደረገላቸው ገልጸዋል። በከተማዋ ቦሌ ክፍለ ከተማ በተመቻቸላቸው የመሥሪያ ቦታ ላይ ከአምስት የቤተሰብ አባላት ጋር በመደራጀት በዚህ ዓመት ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል።   መንግሥት ባመቻቸላቸው የ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ብድር በዳቦ ማምረቻ ኢንተርፕራይዝ ተደራጅተው ምርታቸውን ለአካባቢው ማኅበረሰብ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን አስረድተዋል። አሁን ላይ ከራሳቸው አልፈው ለ10 ተጨማሪ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን አውስተዋል። ሌላኛው በዱቄት ማምረቻ ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ገዙ በዳዳ በበኩላቸው፤ መንግሥት ወደ ልማት እንዲገቡ እንዲሁም ተጠቃሚ እንዲሆኑ ትልቅ እገዛ ማድረጉን ገልጸዋል። ከተማ አስተዳደሩ የመሥሪያ ቦታ ከመስጠትና መሠረተ ልማት ከማሟላት ባለፈ፣ ከባንክ የ2 ሚሊዮን ብር ብድር እና የካፒታል ማሽን አቅርቦት እንዲያገኙ በማመቻቸት በሙሉ አቅማቸው ወደ ሥራ እንዲገቡ ድጋፍ ማድረጉን አመልክተዋል።   አቶ ገዙና የቤተሰባቸው አባላት የዱቄት ማምረቻ ማኅበር በቀን 330 ኩንታል የስንዴ ዱቄት በማምረት ለዳቦ ፋብሪካዎችና ለኅብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ ይገኛሉ ብለዋል። በዚህም ውጤታማ መሆን ከመቻላቸው ባለፈ ለስምንት ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ገልጸዋል።   የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው፤ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የቤተሰብ ብልጽግና ፓኬጅ በከተማዋ በተደራጀ መልኩ ተግባራዊ እየተደረገ ነው ብለዋል። ይህ አሠራር እያንዳንዱን ቤተሰብ ለለውጥና ለዕድገት በማነቃቃት፣ ለመበልፀግ በቁጭት እንዲነሱ ማድረጉን ጠቁመው፤ ተሳታፊዎች የጠራ ግንዛቤ ይዘው ሥራ ውስጥ እንዲገቡ እየተደረገ ይገኛል ነው ያሉት። በበጀት ዓመቱ ለቤተሰብ ብልጽግና ተሳታፊዎች የሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን የጠቀሱት ከንቲባው፤ ለዚህም አስተዳደሩ የመሥሪያና የመሸጫ ቦታዎችን እንዲሁም የብድር አቅርቦትን ለማመቻቸት እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህ ዓመት በከተማዋ በተገነቡ በርካታ ሼዶች 89ሺህ የከተማዋ ወጣቶችና ነዋሪዎች በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዘርፎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆን ችለዋል ብለዋል።
ሀዋሳ ከተማን ለነዋሪዎች ምቹ እና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጠናክሮ ይቀጥላል
May 27, 2026 248
ሀዋሳ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን ለነዋሪዎች ምቹ እና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ከከተማው ከንቲባና ከተለያዩ ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች ጋር በመሆን፤ በከተማዋ ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።   ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በምረቃው መርሃ ገብር እንዳሉት፤ የለውጡ መንግስት ለከተሞች በሰጠው ልዩ ትኩረት የከተሞችን ዕድገት የሚያፋጥኑ ዘርፈ-ብዙ የልማት ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በዚህም ሀዋሳን ለነዋሪዎቿ ምቹ፣ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት ደግሞ ተመራጭ ለማድረግ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ቀጣይነት ለማረጋገጥ ህብረተሰቡን ያሳተፈ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።   በከተማዋ የተመረቁት የልማት ፕሮጀክቶች በኮሪደር ልማት የተጀመሩ ሥራዎችን ከማጠናከር ባለፈ፤ የአገልግሎት አሰጣጥን በማሳለጥ የሕዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች የሚመልሱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የክልሉ መንግስት ሀዋሳን የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ ለቱሪዝም መስህብ ልማቶችና ለአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ማስፋፊያ ልዩ ትኩረት መስጠቱንም አንስተዋል።   የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው፤ የሀዋሳን የኮሪደር ልማትና ሁሉን አቀፍ የልማት ፕሮጀክቶች በማፋጠን ከተማዋን የቱሪዝምና የኢንዱስትሪ ማዕከል ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በከተማዋ በመደመር እሳቤ የሚከናወኑት የልማት ፕሮጀክቶች በተለይም በጥራት ላይ ማተኮራቸውን አብራርተዋል። ዛሬ ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የአዳሬ አጠቃላይ ሆስፒታል ማስፋፊያ፣ የአጠቃላይ ትምህርት ቤቶች ማስፋፊያ ግንባታ እና ሌሎች መሰረተ-ልማቶች ይገኙበታል ብለዋል። እነዚህ ፕሮጀክቶች በአጠቃላይ ከ2 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው መሆኑን ከንቲባው አስታውቀዋል።   የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዋ ሲስተር እልፍነሽ ናኡሼ፤ በሃዋሳ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች ከተማዋን አዲስ ገጽታ እያላበሷት መሆኑንና የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች አዲስ የሥራ ዕድል እየፈጠሩ እንደሚገኙ አክለዋል።   ሌላኛው የከተማው ነዋሪ አቶ ተስፋዬ አበባው፤ ዛሬ በከተማዋ የተመረቁት ፕሮጀክቶች በተለይም በጤናው ዘርፍ የነበሩትን ውስንነቶች ከመቅረፍ አንጻር ትልቅ ሚና እንደሚኖራቸው ገልጸዋል። በምረቃ መርሃ-ግብሩ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር)፣ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎችና የሕብረተሰብ ተወካዮች ተገኝተዋል።
የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የበለጠ ያነቃቃል
May 27, 2026 142
ነገሌ ቦረና፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የበለጠ የሚያነቃቃ መሆኑን የዞኑ ነዋሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የሀገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውንና አዲሱን የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያን ዛሬ በይፋ መርቀዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው እንደ ቦይንግ 737 ማክስ ያሉ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን የማስተናገድ አቅም ያለው ይህ ዘመናዊ አውሮፕላን ማረፊያ፤ የአካባቢውን እንዲሁም ድንበር ተሻጋሪ የንግድ ልውውጥን እና ቱሪዝምን የማሳደግ ራዕይን ሰንቆ በሳምንት ሦስት በረራዎችን የሚያስተናግድ ነው ብለዋል። በምስራቅ ቦረና ዞን የተገነባው ይኸው የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑ፣ ምቹ፣ ፈጣንና ቀልጣፋ የትራንስፖርት አገልግሎት ለማግኘት እንደሚያስችላቸው የዞኑ ነዋሪዎች ገልጸዋል። የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪው እንዳለ መገርሳ እንደገለጹት፤ የአውሮፕላን ማረፊያው በየብስ ትራንስፖርት ረጅም ጉዞ ምክንያት ይደርስ የነበረውን እንግልትና ችግር በእጅጉ ያቃልላል። ዞኑ በእንስሳት ሀብትና የስንዴ ምርት የሚታወቅ ቢሆንም፣ ምርቱን ለማጓጓዝ የትራንስፖርት እጥረት ያጋጥም እንደነበር አስታውሰው፣ አውሮፕላን ማረፊያው የምርት ዝውውርን የበለጠ ያቀላጥፋል ብለዋል። ይህም ለአካባቢው ኢኮኖሚና ቱሪዝም እድገት ካለው አስተዋጽኦ ባሻገር የመንገደኞችን ጉዞ ምቹ፣ ቀላልና ፈጣን እንደሚያደርገው ገልጸዋል። በዘመናዊ ትራንስፖርት ለመጠቀም የነበራቸው ምኞት በመሳካቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል። ሌላው የነገሌ ቦረና ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ ፈንታ ገረመው በበኩላቸው፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ስራ መጀመር የዞኑን ልማትና እድገት እንደሚያፋጥን ገልጸዋል። በተለይም የነገሌ ቦረና ከተማን የንግድና የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አብራርተዋል። ሌላው በዞኑ ሊበን ወረዳ ነዋሪ ቢሉ ቢርቢርሳ የአውሮፕላን ማረፊያው መንግስት ለአርብቶ አደሩ አካባቢ የሰጠውን ትኩረትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት በተግባር ያረጋገጠ መሆኑን አንስተዋል። ለአካባቢው ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል እንደሚፈጥር፣ የግብርና ምርቶችና ግብአቶች በወቅቱና በፈጣን ሁኔታ እንዲጓጓዙ እንደሚረዳና ባለሀብቶች እንዲሁም ተጓዦች ወደ ዞኑ በቀላሉ እንዲመጡ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ጠቅሰዋል። በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ የሀገር ሽማግሌዎች፣ አባገዳዎች፣ የፌደራል፣ የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በርካታ ቁጥር ያለው የዞኑ ህዝብ ተገኝቷል።
የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ መመረቅ ፍትሐዊና ሚዛናዊ የመሠረተ ልማት ዝርጋታን የሚያረጋግጥ ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 194
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፦ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ መመረቅ ፍትሐዊና ሚዛናዊ የመሠረተ ልማት ዝርጋታን የሚያረጋግጥ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን የገለጹት የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የሀገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውን ይህንን ዘመናዊ አውሮፕላን ማረፊያ በዛሬው ዕለት መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ባደረጉበት ወቅት ነው።   ጠቅላይ ሚኒስትሩ በንግግራቸው ላይ በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ በሁሉም አቅጣጫዎች ትላልቅ አውሮፕላኖችን ማስተናገድ የሚችሉ ወደ 30 የሚጠጉ የአየር ማረፊያዎች እንደሚገኙ ጠቁመዋል። የአየር ማረፊያዎቹ ስርጭት ሀገራዊ አንድነትን እና ልማትን እኩል ለማስፈን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ገልጸው፤በሰሜን 10፣ በምሥራቅ 5፣ በምዕራብ 7 እንዲሁም በደቡብ የሀገሪቱ ክፍል አዲሱን የነገሌ ገዳ አውሮፕላን ማረፊያን ጨምሮ 6 የአየር ማረፊያዎች መኖራቸውን በዝርዝር አብራርተዋል። የቦረና ሕዝብ የኦሮሞን ማንነት፣ባህልና እሴት ጠብቆ ያቆየ እንዲሁም ከጉጂና ባሌ ማኅበረሰቦች ጋር በትብብር የኖረ ታላቅ ሕዝብ መሆኑን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለሰላም ወዳዱ የቦረና እና ጉጂ ሕዝብ ልማት ብንዘገይም ደርሰንለታል ብለዋል።   አዲሱ የመሠረተ ልማት አውታር አካባቢው ከአዲስ አበባ ካለው የርቀት ስፋት አንጻር የሚፈጥረውን ተግዳሮት በመቅረፍ፤ ለአካባቢው ማኅበረሰብ ዘርፈ-ብዙ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የገነባው ይህ አዲስ አውሮፕላን ማረፊያ እንደ ቦይንግ 737 ማክስ ያሉ ዘመናዊና ግዙፍ አውሮፕላኖችን የማስተናገድ ሙሉ አቅም እንዳለውም ተናግረዋል። በሳምንት ሦስት የበረራ ቀናትን የሚያስተናግደው ይህ አየር ማረፊያ፤ የክልሎችን ኢኮኖሚያዊ አቅም ከማነቃቃት ባለፈ የድንበር ተሻጋሪ የንግድ ልውውጥንና የቱሪዝም ዘርፍን ለማሳደግ ታላቅ ራዕይ የሰነቀ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል። የአየር ማረፊያውን ለገነባው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። በቀጣይም ፍትሐዊ ተጠቃሚነትንና የገበያ ትስስርን መሠረት ያደረጉ አዳዲስ የአየር ማረፊያዎች ግንባታ በተለይም በደቡብና ምሥራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች ተጠንተው እንደሚቀጥሉም ጠቁመዋል። ለዚህም ስኬት ሰላም ወዳዱ የጉጂና የቦረና ሕዝብ የጀመረውን የልማት ትብብር አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
የቦረና ሕዝብ ከተረጅነት ነፃ መውጣቱ በተግባር የታየ ትልቅ ለውጥ ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 181
አዲስ አበባ፤ግንቦት 19 /2018 (ኢዜአ)፦የቦረና ሕዝብ ያሳየው የታታሪነትና የሥራ ወዳድነት መንፈስ የተፈጥሮ ጸጋን ተጠቅሞ ከረሃብ መውጣት እንደሚቻል ትልቅ ማረጋገጫ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ያመለከቱት በምስራቅ ቦረና ዞን ሊበን ወረዳ በሜካናይዜሽን የታገዘውንና በክላስተር እየለማ የሚገኘውን ሰፊ የስንዴ ማሳ በጎበኙበት ወቅት ነው።   የአካባቢው ማህበረሰብ ከጥቂት ዓመታት በፊት ይደርስበት ከነበረው ተደጋጋሚ የድርቅ አደጋና የውኃ እጥረት ፈተና ተላቆ፣ በአሁኑ ወቅት በአረንጓዴ ልማት አዲስ ምዕራፍ እየጻፈ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል። ቀደም ሲል እስከ 90 በመቶ የሚደርሰው የዞኑ ነዋሪ በሴፍቲኔት ድጋፍ ይተዳደር እንደነበርና ማህበራዊ ሁነቶች እንኳ ሳይቀሩ በእርዳታ እህል ይከናወኑ እንደነበር ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ዛሬ ላይ ግን ያ የድህነት ታሪክ ተቀይሮ የተረጅነት ምጣኔው ወደ ዜሮ መውረዱን ይፋ አድርገዋል። ይህ በአጭር ጊዜ ውስጥ የተመዘገበውና ማህበረሰቡን ከእርዳታ ጥገኝነት ሙሉ በሙሉ ያላቀቀው ስኬት በቃላት ሊገለጽ የማይችል ተዓምር መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮው አውድማ በሊበን ወረዳ ብቻ 250 ሺህ ሄክታር መሬት በስንዴ ሰብል መሸፈኑን ጠቁመው፤ የተሻሻሉ የውኃ አማራጮችን በመጠቀም ምርታማነቱን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚቻልና ይህም ከአገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ምርትን ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ዕድል እንደሚፈጥር አመላክተዋል። ቀደም ሲል የረድኤት እህል ይከፋፈልበት የነበረው ስፍራ ዛሬ ወደ ሰፊ የምርት ማዕከልነት ተለውጦ ማየት ታላቅ ደስታን የሚፈጥር መሆኑን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህ አይነቱ አመርቂ የልማት ተሞክሮ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎችም ሊሰፋ እንደሚገባ አሳስበዋል። በርትቶ በመስራት ከልመናና ከረሃብ መውጣት እንደሚቻል የቦረና ሕዝብ በተግባር ማሳየቱንም አክለዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማጠቃለያቸው፤ የቦረና ሕዝብ ያሳየው ታታሪነት እና የስራ ወዳድነት መንፈስ የተፈጥሮ ጸጋንና እውቀትን አቀናጅቶ በመጠቀም ረሃብንና ጥገኝነትን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስወገድ እንደሚቻል ትልቅ ማረጋገጫ የሰጠ ነው ብለዋል።
በምሥራቅ ቦረና ዞን እየታየ ያለው የግብርና ትራንስፎርሜሽን፤ ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ለመቻል ለምታደርገው ጉዞ ትልቅ ማረጋገጫ ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 229
አዲስ አበባ፤ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፦በምሥራቅ ቦረና ዞን እየታየ ያለው የግብርና ትራንስፎርሜሽን፤ ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ለመቻል ለምታደርገው ጉዞ ትልቅ ማረጋገጫ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት፥ በዚህ ወቅት ብቻ ታታሪ አርሶአደሮች ከ176,223 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ላይ እንደሚገኙና ከዚህም ከ3.1 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚያገኙ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል።   ይህ የእርሻ ልማት ሥራ ከ101,000 በላይ አባወራዎችንና እማወራዎችን በማሳተፍ እንዲሁም ዘመናዊ ትራክተሮችን በመጠቀም እየተከናወነ እንደሚገኝ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በተደራጀ የክላስተር እርሻ አማካኝነት እምቅ አቅማችንን ወደ ምርታማነት እየቀየርን እንገኛለን ብለዋል።   በምሥራቅ ቦረና ዞን ሊበን ወረዳ ከሚገኙት ሰፋፊ የስንዴ ክላስተሮች ጀምሮ እስከ ዋና ዋናዎቹ የጤፍ፣ የበቆሎ እና የቦሎቄ ምርቶች ድረስ እየታዬ ያለው ውጤት፤ የሀገር ውስጥ የምግብ አቅርቦታችንን የማረጋገጥ ጉዞ ላይ ለመገኘታችን ህያው ምስክር መሆኑንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
በክልሉ ሰላምን በማጽናት የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን በቅንጅት ማሳካት ተችሏል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
May 26, 2026 611
ደሴ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ሰላምን በማጽናት የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን በቅንጅት ማሳካት መቻሉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለፁ። በደሴ ከተማ አስተዳደር በ1 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በምረቃው ወቅት እንደገለፁት፤ የክልሉን ሰላም በማጽናት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ሰፋፊ የልማት ፕሮጀክቶችን በመገንባት ለውጤት እንዲበቁ ተደርጓል።   የልማት ፕሮጀክቶቹን በቅንጅት በማሳካት የህብረተሰቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በየደረጃው ለመመለስ ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ገልጸዋል። የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ፣ የገበያ መረጋጋትን ለማምጣት፣ የስራ እድልን ለመፍጠር፣ የትምህርትና የጤናው ዘርፍ ተደራሽነትን ለማሳደግ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። የክልሉን እድገት በማረጋገጥ ወደ ሁለተናዊ ብልጽግና የማሸጋገር ተግባራት በቅንጅት እንደሚከናወኑ ጠቁመው በደሴ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር ልማት፣ የአስፋልት መንገድና ሌሎች የመሰረት ልማት ግንባታዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሳሙኤል ሞላልኝ በበኩላቸው የከተማውን ሰላምና ልማት ዘላቂ ለማድረግ ህብረተሰቡን ያሳተፉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን ጠቁመዋል።   በዚህም በከተማው የአስፋልት መንገድ፣ የኮሪደር ልማት፣ የመናኸሪያ፣ የፍሳሽ ማስወገጃ፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ፣ የትምህርት ቤት ማስፋፊያና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ተጠናቅቀው ዛሬ ለምርቃ በቅተዋል ብለዋል። የልማት ስራዎቹ መንግስት ለሰው ተኮር ፕሮጀክቶች በሰጠው ትኩረት የተከናወኑ መሆናቸውን ገልጸው የማህበረሰቡን ተጠቃሚነትም አሳድገዋል ነው ያሉት። በምረቃ መርሃ ግብሩ የአማራ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋዬ፣ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)ን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተገኝተዋል።
የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ አስችሎናል - ሸማቾች
May 26, 2026 246
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በየአካባቢው መስፋፋታቸው የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ አስችሎናል ሲሉ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በተለያዩ አካባቢዎች ላይ ሕብረተሰቡ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ በማድረግና ገበያን በማረጋጋት በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑ ይታወቃል። በዚህም የተለያዩ የግብርና ምርቶችን ጨምሮ የተለያዩ ሸቀጦች በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረቡ ይገኛሉ። በጉዳዩ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው አስተያየት ሰጪዎች እንደገለጹት፤ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በአቅራቢያችን በመጀመሩ የግብይት ስርዓቱን ቀልጣፋ እና ምቹ አድርጎታል።   አስተያየት ከሰጡ ሸማቾች መካከል ወይዘሮ ገነት አድማሱ፤ ገበያው በአቅራቢያችን በመከፈቱ የፍጆታ እቃዎችን በቀላሉ በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት አስችሎናል ብለዋል። ይህ አይነት ገበያ መኖሩ ለነዋሪዎች ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎትን ከማግኘት ባለፈ የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት ትልቅ አስታዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል።   ወይዘሮ ጸጋ አዱሽ በበኩላቸው፤ በቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች የአትክልትና ፍራፍሬ በብዛት ከመቅረቡ ባሻገር ሰፊ አማራጮች የሚገኙበት ነው ብለዋል። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በየአካባቢው መኖሩ ለአቅመ ደካሞችና ረጅም መንገድ ተጉዘው መገበያየት ለማይችሉ ትልቅ ጥቅም እንዳለው ገልጸው፤ ገበያው ላይ በተመጣጣኝ ዋጋ እንደሚያገኝ የገለጸችው ደግሞ ማአዛነሽ መለሰ ናቸው።   በቅዳሜ እሁድ ገበያዎች ምርቶቻቸውን ይዘው የቀረቡ ነጋዴዎች በበኩላቸው፤ ጥራቱን የጠበቀ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አስተያየታቸውን ካጋሩን መካከል እየሩሳሌም ሐብቶም፤ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በበርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች ነዋሪዎች ተፈላጊነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል ብለዋል።   ይህን ፍላጎት ለማሟላት ጥራት ያላቸውን ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ እያቀረቡ መሆኑን ነው የሚናገሩት።   ሌላኛዋ ነጋዴ ቤተልሔም አዱኛ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የዋጋ ንረትን በመቀነስ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማስፋት መጀመሩን ገልጸው፤ ከመደበኛ ሱቆች ከፍተኛ ልዩነት እንዳለው ጠቁመዋል። በአዲስ አበባ ሸማቾች በቀላሉ በአቅራቢያቸው መገብየት የሚያስችሉ በሁሉም አካባቢዎች 250 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች አሉ።  
ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማትን ይበልጥ ተወዳዳሪ አድርጓል
May 26, 2026 286
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማትን ይበልጥ ተወዳዳሪ ለማድረግና የህብረተሰብ ተሳትፎን ለማሳደግ ያስቻለ መሆኑን የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ ገለፁ። የካፒታል ገበያ ለሀገሪቱ ኩባንያዎች የረጅም ጊዜ ካፒታል ምንጭ የሚያስገኝና የፋይናንስ አማራጭን በማስፋት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መረጋጋት የሚደግፍ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮ-ቴሌኮም በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ መመዝገቡን ይፋ ያደረገ ሲሆን ይህም ባለአክሲዮኖች በሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ አክስዮናቸውን እንዲያስተዳድሩ፣ እንዲገዙና እንዲሸጡ የሚያስችል ነው።   በምዝገባ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ፣ የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጥላሁን እስማኤል (ዶ/ር)፣ የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እንዲሁም የብሔራዊ ባንክና የሌሎች ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ እንደገለጹት፤ ሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ የኢኮኖሚ መዋቅሩን ማዘመን፣ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማሳደግ፣ የመንግሥት ልማት ድርጅቶችን ተወዳዳሪነትና የሕብረተሰቡን ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል ነው። የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማት ለበርካታ ዓመታት ሙሉ በሙሉ በእጅ ስር እንደነበሩ አስታውሰዋል። የኢኮኖሚ ማሻሻያው ይህን አካሄድ በመቀየር ተቋማቱ ይበልጥ ተወዳዳሪ እንዲሆኑና የህዝብ ተሳትፎ እንዲያድግ በር ከፍቷል ብለዋል። በዚህም ኢትዮ-ቴሌኮም የባለቤትነት ይዞታውን ክፍት በማድረግ የመጀመሪያው የመንግስት የልማት ድርጅት በመሆን በሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ በይፋ መመዝገቡን ተናግረዋል። ምዝገባው ለወራት ሲካሄድ የቆየ የዝግጅት ውጤት መሆኑን ጠቅሰው ባለስልጣኑ ሂደቱ ግልፅነትና ዓለምአቀፍ አሰራር የተከተለ እንዲሁም የኢንቨስተሮችን መብት የሚያስጠብቅ እንዲሆን ሲሰራ መቆየቱን አስታውቀዋል። የካፒታል ገበያ መመስረትና ማደግ በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎችን የሀገሪቱ ግዙፍ ድርጅቶች ባለድርሻ የሚያደርግ ነው ብለዋል። የካፒታል ገበያ ለሀገሪቱ ኩባንያዎች የረጅም ጊዜ ካፒታል ምንጭ የሚያስገኝና የፋይናንስ አማራጭን በማስፋት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መረጋጋት እንደሚደግፍም ተናግረዋል። በሂደት ላይ ያሉ ተቋማትም የድርጅት አስተዳደራቸውን በማሻሻል ወደዚህ መድረክ እንዲመጡና የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ምህዳር ይበልጥ እንዲሰፋና አማራጭ የካፒታል ምንጭ ለማግኘት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።   የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጥላሁን እስማኤል (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮ- ቴሌኮም ወደ ዘመናዊ የሰነደ ሙዓለ ነዋይ ግብይት መግባት ለሥራቸው ታላቅ አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። አያይዘውም ባለአክሲዮኖች ወደ ዘመናዊ የኤሌክትሮኒክስ መገበያያ ሥርዓት መግባታቸውንና የንግድ አካውንት በመክፈት በአገናኝ አማካኝነት መገበያየት እንደሚችሉ ጠቁመዋል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ፤ ኢትዮ-ቴሌኮም የ10 በመቶ ድርሻውን ለዜጎች መሸጡን ተከትሎ የባለአክሲዮኖችን መረጃ የመሰነድና የማደራጀት ሥራ በማከናወን በኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን አጸድቋል ብለዋል።   በዚህም አክሲዮን ከገዙ 47ሺህ 377 ባለአክሲዮኖች 10 ነጥብ 7 ሚሊዮን አክሲዮኖችን በመሸጥ 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። ከእነዚህ መካከል የ45 ሺህ ያህሉ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ 10 ነጥብ 1 ሚሊዮን አክሲዮን በ3 ቢሊዮን ብር ለባለ አክሲዮንነት ብቁ ሆነው በመገበያያ ማዕቀፉ መካተታቸውን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት የ96 በመቶ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ የዲጂታል ባለቤትነት ማረጋገጫ ማግኘት መቻላቸውን ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም መድረክ ጠንካራ የተወዳዳሪነት አቅም የገነባ ተቋም ነው - አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ
May 26, 2026 262
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም መድረክ ጠንካራ የተወዳዳሪነት አቅም የገነባ ተቋም መሆኑን በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከቀናት በፊት የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን በተለያዩ ሆነቶች በደማቅ መርሃ ግብር አክብሯል። በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት ተቋማዊ ዕድገትን ማስቀጠል እያስቻሉት ነው። አየር መንገዱ በገነባው የረጅም ዘመናት ዓለምአቀፍ ስምና ዝናም ከአሜሪካ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ኩባንያዎች ጋር ጠንካራ የትብብር አጋርነት እንዳለው ገልጸዋል። ለአብነትም በዓለም አቀፍ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሆኑት ከቦይንግና ጂኢ-ኤሮስፔስ የአሜሪካ ኩባንያዎች ጋር ጥብቅ አጋርነት ያለው ተቋም መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ዘርፍ አፍሪካን ከቀሪው ዓለም የሚያስተሳስር አስደናቂና ግዙፍ መሰረተ ልማት በማስፋፋት ላይ የምትገኝ ሀገር መሆኗንም አንስተዋል። በዚህም የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአዳዲስ የመንገደኛ አውሮፕላን፣ የበረራ መዳረሻ በማስፋትና በሀገር ውስጥ የአየር ማረፊያ መሠረተ ልማት ግንባታ አስደናቂ ሥራ እየሰራ መሆኑን አብራርተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የገነባው አቅም ቀጣናዊ አየር መንገድ ብቻ ሳይሆን በዓለም መድረክ ላይ ተወዳዳሪ እንዲሆን ማስቻሉን ገልጸዋል። የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅትን ጨምሮ በአስቸጋሪ ወቅቶች በአሜሪካና በኢትዮጵያ አየር መንገድ መካከል የተገነባው ጠንካራ ግንኙነት ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። በኮቪድ ወረርሽኝ ወቅትም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከአሜሪካ ጋር የነበረው ጠንካራ ትብብርና አጋርነት የክትባትና መድኃኒት ቁልፍ ቁሳቁሶችን በማጓጓዝ ከፍተኛ ሚና እንዲወጣ ማስቻሉን አስታውሰዋል። የአየር መንገዱ የወደፊት ዕቅድና የአቅም ግንባታ የትኩረት መስክ ለቀጣይ ስኬቱ ቁልፍ እንደሚሆኑም አምባሳደሩ ጨምረው ገልጸዋል። በዚህም በኢትዮጵያ አየር መንገድ የዕድገት ጉዞ ላይ አሜሪካና የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ኩባንያዎቿ አጋርነታቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በኢትዮጵያና አሜሪካ መካከል ያለው ታሪካዊ ግንኙነት በተለያዩ የልማትና የትብብር መስኮች እየተጠናከረና እያደገ መምጣቱን አስረድተዋል።
በኦሮሚያ ክልል ከተሞች የማህበረሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት ተደርጓል
May 26, 2026 122
መቱ፣ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ከተሞች የነዋሪውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ላይ በትኩረት በመሰራቱ የተሻለ ውጤት መገኘቱ ተገለጸ። በመቱ ከተማ ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 48 የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል።   በክልሉ ከተሞች የሚከናወኑ የሕንጻዎችና የመሠረተ ልማት ግንባታዎች ምቹ የመኖሪያና ማሕበራዊ አካባቢዎችን ለመፍጠር፣ የመሠረተ ልማት አውታሮችን ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም ቀልጣፋና ዘመናዊ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓትን ለማስፈን ያለሙ መሆናቸውም ተገልጿል። በምረቃ መርሐግብሩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ግርማ ረጋሳ እንደገለጹት፤ በክልሉ ከተሞች በቂ የመሰረተ ልማት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። ፍትሐዊና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓት ከማስፈንና የማሕበረሰቡን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አንጻር በርካታ ተግባራት መከናወናቸውንም ጠቁመዋል። ኃላፊው አክለውም፣ በክልሉ በየጊዜው እየተገነቡ ለአገልግሎት ክፍት የሚሆኑ የልማት ፕሮጀክቶች ዜጎች የተሻለ ሕይወት እንዲመሩ የሚያስችሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል።   የመቱ ከተማ ከንቲባ አቶ ተሻለ ኤጄርሶ በበኩላቸው፣ ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት 48 ፕሮጀክቶች መካከል የትምህርት ቤቶች ግንባታና የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶችን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የመንገድ ዳር የኮሪደር ልማት ስራዎች፣ የንግድ መስሪያ ቦታ ሼዶች፣ የከተማ ግብርና ማዕከላት፣ የኤሌክትሪክ መስመሮች ዝርጋታ እና የከተማ አስተዳደር ሕንጻም መመረቁን ተናግረዋል። ከንቲባው ፕሮጀክቶቹ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ከማዘመንና ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ፣ የሕብረተሰቡን ማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግና ከተማዋን ውብና ምቹ የመኖሪያ አካባቢ ለማድረግ የሚረዱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የመቱ ከተማ ነዋሪዎች መካከል አቶ አብዱራህማን ኢድሪስ እና አቶ ተስፋዬ ኮንቺ ግንባታው ተጠናቆ ወደ አገልግሎት የገባው የከተማ አስተዳደሩ ሕንጻ የከተማዋን ገጽታ የሚያሳድግ ከመሆኑም በላይ፣ ቀልጣፋ፣ ዘመናዊና ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። ወይዘሮ ኑሪያ ሁሴን እና አቶ መሐመድጣሂር አባገሮ በበኩላቸው የተገነቡት ሼዶች የሥራ ዕድል የሚፈጥሩና ሠርተው የሚለወጡበትን ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው ብለዋል። የመንገድ ዳር የኮሪደር ልማቱ የትራፊክ ፍሰቱ የተሳለጠ እንዲሆንና አደጋ እንዲቀንስ ከማድረጉም በላይ፣ የከተማዋን ውበት በመጨመር ለመኖሪያነት ምቹ አድርጓታል ብለዋል።  
የከተማውን አገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን ለንግድና ኢንቨስትመንት የበለጠ ምቹ ለማድረግ ትከረት ተሰጥቷል
May 26, 2026 185
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በወላይታ ሶዶ ከተማ የመንግስት አገልግሎትን በማዘመን ከተማውን ለንግድና ኢንቨስትመንት የበለጠ ምቹ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ ። የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር ከ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ለሚያስገነባው የባለ 12 ወለል የቢሮ ሕንፃ ግንባታ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ዛሬ ተካሂዷል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ በወቅቱ እንደገለጹት የወላይታ ሶዶ ከተማ ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ እየሆነች መምጣቷን ተከትሎ አገልግሎት አሰጣጡን ማዘመን አስፈልጓል። ግንባታው የተጀመረው የከተማ አስተዳደሩ የቢሮ ህንጻ ምቹ የሆነ የስራ አካባቢ በመፍጠር የመንግስት አገልግሎት አሰጣጡን ለማዘመን የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል ። የአገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን ከተማዋን ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ ለማድረግ በሚደረገው ሂደት በቅንጅትና በትብብር መስራት አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል።   የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማርያም በከተማ አስተዳደሩ ምቹ የስራ አካባቢ ለመፍጠር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የሚገነባው ዘመናዊ የቢሮ ህንፃ የዚሁ አካል መሆኑን ጠቁመው ህንጻው ከተማዋን ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭና ተወዳዳሪ ለማድረግ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል፤ የቢሮ ህንጻው በ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር የሚገነባ መሆኑን ጠቁመው ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ አስታውቀዋል ።      
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም