ኢኮኖሚ
በሐረሪ ክልል በበጀት ዓመቱ 10 ወራት ከ1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰበሰበ
Jun 3, 2023 22
ሐረር ግንቦት 26/2015(ኢዜአ)፡- በሐረሪ ክልል በ2015 በጀት ዓመት 10 ወራት ከተለያዩ የገቢ ምንጮች ከ1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ አቶ በቀለ ተመስገን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ የታቀደውን የልማት ስራ ለማሳካት የገቢ አሰባሰብ ስርዓትን በማዘመን በኩል በትኩረት እየተሰራ ነው። የልማት እቅዶቹን ለማሳካት ቢሮው በተለይ የአገልግሎት አሰጣጥን በማጎልበትና በቴክኖሎጂ የተደገፉ አሰራሮችን በማመቻቸት የገቢ አሰባሰብ ስርዓቱት ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ በበጀት ዓመቱ ያለፉት አስር ወራት ከቀጥታና ቀጥታ ካልሆነ ታክስ እንዲሁም ታክስ ነክ ካልሆነና ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ከ1 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ ተሰብስቧል። ይህም አፈጻጸሙ ከእቅዱ በላይ እንደሆነና ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ደግሞ በ44 ነጥብ 6 በመቶ ብልጫ እንዳለው ነው የቢሮ ኃላፊው ያመለከቱት። ገቢው በብልጫ የተሰባሰበው በተለይም ከግብር አሰባሰብ ጋር በተያያዘ የአገልግሎት አሰጣጥ ስራዎች በማዘመን በደረሰኝ አቆራረጥ ላይ የተጠናከረ ክትትልና ቁጥጥር መደረጉ፣ውዝፍ ክፍያዎች በመሰብሰባቸውና ወደ ሕጋዊ ንግድ የሚገቡ ነጋዴዎች ቁጥር በመጨመሩ ነው ብለዋል። እንዲሁም በክልሉ “ከየካቲት እስከ የካቲት” በሚል መሪ ሀሳብ የተጀመረው የግብር ንቅናቄ ለገቢው መጨመር አስተዋጽኦ ማድረጉን አስረድተዋል። የሚሰበሰበው ገቢ የክልሉን ነዋሪ የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን እየደገፈ ይገኛል ነው ያሉት። በበጀት ዓመቱ ቀሪ ወራት የክልሉ ገቢን ለማሳደግ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አቶ በቀለ ገልጸዋል። ከክልሉ ግብር ከፋዮች መካከል በሸቀጣ ሸቀጥ ንግድ የተሰማሩ አቶ ጌታቸው ፍቅሩ በሰጡት አስተያየት፤ ግብር ካልተከፈለ ልማት የለም ብለዋል።   ከዚህ ቀደም ግብርን ለመክፈል በቢሮው በኩል ይታዩ የነበሩ የአሰራር ክፍተቶች በአሁኑ ወቅት ተሻሽሎ የተቀላጠፈ አገልግሎት እያገኙ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በሐረር ከተማ በሆቴል ስራ የተሰማሩት አቶ ደሳለኝ አስፋው ለአገርና ለሕዝብ ልማት መሰረት የሆነውን ግብርን ሁሉም ዜጋ በተነሳሽነት በመክፈል ግዴታውን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።   በሐረሪ ክልል ከ27 ሺህ በላይ ግብር ከፋዮች እንዳሉ ከክልሉ ገቢዎች ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።        
ታዳሽ የኃይል አማራጮችን በመጠቀም የኤሌክትሪክ አገልግሎትን ለዜጎች ለማዳረስ እየተሰራ ነው-የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር
Jun 2, 2023 50
ሆሳዕና ግንቦት 25/2015 ( ኢዜአ )፡- በኢትዮጵያ ያሉትን ታዳሽ የኃይል አማራጮችን በመጠቀም ለዜጎች የኤሌክትሪክ አገልግሎትን ለማዳረስ እየተሰራ መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ገለጸ። በሚኒስቴሩ የኢነርጂ ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ እና ሌሎች የተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች በሀድያ ዞን ግቤ ወረዳ ገሰጣ ኦዳዳ ቀበሌ እየተገነባ ያለውን የኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ጎብኝተዋል።   ለሁሉም አካባቢ ከዋናው የኤሌክትሪክ መስመር(ግሪድ) አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ አመቺ ባልሆኑ አካባቢዎች ያሉ አቅሞች ላይ የተመሰረተ የታዳሽ ኃይል አማራጭን በመጠቀም የኤሌክትሪክ አገልግሎትን ተደራሽነት ለማስፋፋት ጥረት እየተደረገ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል። ለዚህም በሀዲያ ዞን ጊዜ ወረዳ ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ በጀት እየተነገባ ያለው ኃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግንባታ ፕሮጀክት በማሳያነት ጠቅሰዋል። ይህም ከ20 ኪሎ ዋት በላይ ኃይል የማመንጨት አቅም እንዳለው እና ከኃይል አቅርቦት ባሻገር ለግብርናና ለሌሎች የልማት አገልግሎቶች ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ከ65 ሚሊዮን በላይ የኤሌክትሪክ ኃይል ለማያገኘው ሕዝብ አገልግሎቱን ተደራሽ ለማድረግ የታዳሽ ኃይል አማራጭን መጠቀም የመጀመሪያው አማራጭ መሆኑን ተናግረዋል። ታዳሽ የኃይል አማራጭን በመጠቀም የዜጎችን የኤሌክትሪክ ፍላጎት ለማሟላት የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን በአገር ውስጥ መጠቀም የሚያስችል እድል አለ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው። የውሃ እና የፀሐይ ኃይል የተፈጥሮ ፀጋዎች በመጠቀም ዜጎች የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲያገኙ ለማድረግ ይሰራል ብለዋል። የሀድያ ዞን ውሃ መስኖና ኢነርጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ መለሰ ኃይሌ የታዳሽ ኃይል አማራጮችን መጠቀም የዛፍ ጭፍጨፋን ለማስቆም እና የእናቶችን ጊዜ እና ጉልበት ለመቆጠብ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል።   የዜጎችን የኤሌክትሪክ የኃይል ፍላጎትና የአቅርቦት ውስንነትን ችግርን በዘላቂነት ለመፍተት ሚኒስቴሩ ለቴክኖሎጂው የተሰጠው ትኩረት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል። በአካባቢያቸው በኤሌክትሪክ አገልግሎት ተደራሽነት ችግር ተማሪዎች ኩራዝን በመጠቀም ትምህርታቸውን ተከታትለው አመርቂ ውጤት ለማምጣት ምቹ ሁኔታ እንዳልነበረ የተናገሩት በግቤ ወረዳ የገሰጣ ኦዳዳ ቀበሌ አርሶ አደር ግርማ አላሮ ናቸው። በሚኖሩበት ቀበሌ ያለምንም ጥቅም ከዓመት እስከ ዓመት የሚፈሰውን የ"ለመሬ" ወንዝን በመጠቀም በአካባቢያቸው የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽ እንዲሆን እየተደረገ ያለው ጥረት አስደሳች መሆኑን ገልጸዋል።   የኃይል ማመንጫው አገልግሎት እስከሚጀምር ድረስ በጉጉት እየጠበቁ እንደሚገኙም ተናግረዋል። የአካባቢው ማህበረሰብ ከሁለት ወራት በኋላ ኤሌክትሪክ አገልግሎት እንደሚያገኝ ተገልጿል። በመስክ ምልከታው ላይ የፌዴራል እና የሀድያ ዞን ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።    
የኢትዮጵያ ዳያስፖራዎች በሀገሪቱ የልማት ተሳትፏቸውን ለማሳደግ እየተሰራ ነው- የዳያስፖራ አገልግሎት
Jun 2, 2023 86
ባህርዳር ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፡- በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የሀገሪቱን ልማት ለማፋጠን እያደረጉት ያለውን ተሳትፎ ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ገለጸ። አገልግሎቱ ከአማራ ክልል ጋር በመተባበር የዳያስፖራውን ተሳትፎ ለማሳደግ ያዘጋጀው የምክክር መድረክ ዛሬ በእንጅባራ ከተማ ተካሄዷል።   የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ተወካይ አቶ መላኩ ዘለቀ በመድረኩ ላይ፤ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ በሀገሩ ሰላምና ልማት ወደ ኋላ እንደማይል ገልጸው፤ ባለፉት ዓመታት ዳያስፖራው በፐብሊክ ዲፕሎማሲ የኢትዮጵያን ገጽታ በመገንባትና ሀገሪቱ በችግር ውስጥ በነበረችበት ወቅት በ" ኖ ሞር" እንቅስቃሴ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስታውሰዋል። በተጨማሪም በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ በኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ የልማት ዘርፎች በኢንቨስትመንት በመሳተፍ በስራ እድል ፈጠራና ሀገርን በማሳደግ የበኩሉ የድርሻውን እየተወጣ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ይህም ዕውቀትን፣ ክህሎትንና የቴክኖሎጂ ሽግግርን እንዲሁም አዳዲስ አሰራሮችን ወደ ሀገር በማምጣት ለወጣቱ ትውልድ ለማስተላለፍ ጥረት ማድረጉን ጠቅሰዋል። ይህም ሆኖ ካለው የዳያስፖራ ቁጥርና አቅም አንጻር ሲታይ ሀገሪቱ ከዳያስፖራው የሚገባትን ያህል ጥቅም አግኝታለች ብሎ መናገር እንደማይቻል ተናግረዋል። በመሆኑም በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የሀገሪቱን ልማት ለማፋጠን እያደረጉት ያለውን ተሳትፎ ይበልጥ ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ሰላማዊት አለማየሁ፤ በውጭ የሚኖሩ ዳያስፖራዎች የውጭ ምንዛሬ ወደ ሀገር ውስጥ በመላክ፣ ንግድና ቱሪዝሙን በማስፋፋትና የሀገሪቱን ገጽታ በመገንባት በኩል ዳያስፖራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ማስመዝገባቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም እውቀታቸውን ፣ገንዘባቸውንና ልምዳቸውን ተጠቅመው በክልሉ ብሎም በሀገሪቱ ውስጥ መዋዕለ ንዋያቸውን በማፍሰስ ራሳቸውንና ህዝባቸውን ለመጥቀም በሚያደርጉት እንቅስቃሴ የክልሉ መንግስት ድጋፍ እንደማይለያቸው አስታውቀዋል። ለዚህም መሰል የምክክር መድረክ መልካም ጅምሮችን አጠናክሮ ለማስቀጠልና የታዩ ክፍተቶችን ለይቶ ለማስተካከል እንደሚያግዝ ጠቅሰዋል። በመድረኩ የተሳተፉ የመንግስትና የዳያስፖራ አካላትም በምክክራቸው ለቀጣይ ስራ አቅጣጫ በማስቀመጥ መረባረብ እንደሚጠበቅባቸውም ጠቁመዋል። በምክክር መድረኩ ከፌዴራል፣ ከክልልና ከሁሉም ዞኖች የተውጣጡ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል።  
በሳይንስ ሙዚየም የተዘጋጀው የግብርና አውደ ርዕይ በዘርፉ ልምድ ለመለዋወጥ እድል ፈጥሯል - የጋምቤላ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ኃብት ልማት ቢሮ
Jun 2, 2023 57
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፦ በሳይንስ ሙዚየም የዘጋጀው የግብርና አውደ ርዕይ በዘርፉ ልምድ ለመለዋወጥ እድል የሚፈጥር መሆኑን የጋምቤላ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ኃብት ልማት ቢሮ ገለጸ። የጋምቤላ ክልል አመራሮችና የፌዴራል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በሳይንስ ሙዚየም የቀረቡ የግብርና ውጤቶችን፣ የዘርፉ ቴክኖሎጂ እንዲሁም በሳይንስ ሙዚየሙ የተዘጋጀውን የጋምቤላ ክልል የግብርና አውደ ርዕይን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። የጋምቤላ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ኃብት ቢሮ ኃላፊ አጃክ ኡቻላ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት ክልሉ የግብርናው ዘርፍ ምርትና ምርታማነት ለመጨመር እየሰራ ነው። አውደ ርዕዩ የቀረቡ የፈጠራ ሥራዎችና ቴክኖሎጂዎች ክልሉ ያለውን እምቅ የተፈጥሮ ኃብት በዘመናዊ መንገድ ለመጠቀም የሚያስችል ልምድ ያገኙበት መሆኑን ጠቁመዋል። በመሆኑም አውደ ርዕዩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ለመጠቀምና የዘርፉን ምርትና ምርታማነት ለማረጋገጥ መነሳሳት የሚፈጥርና ልምድ የተቀሰመበት መሆኑን ነው የገለጹት። ያም ብቻ ሳይሆን በዘርፉ ከተሰማሩ ኩባንያዎች ጋር ትስስር ለመፍጠር እንዲሁም ክልሉ በዘርፉ ያለውን አቅምና ኃብት ለማስተዋወቅም እድል የፈጠረ መሆኑን ጠቁመዋል።   በጉብኝቱ ላይ የተገኙት የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ዴኤታ አለሚቱ ኡሞድ በበኩላቸው ጋምቤላ ከፍተኛ ሃብት ያለው ክልል ነው። ይህንንም ዘርፍ በማልማት ለክልሉም ሆኖ ለአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ እድገት የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ ጠቁመዋል። በመሆኑም በቀጣይ የክልሉን ግብርና በማዘመን ምርታማነት ከማሳደግ ባለፈ የገበያ ትስስር መፍጠር ላይ መንግሥትና ባለሃብቱ ትኩረት ሰጥተው እንዲሰሩ ጠይቀዋል። በተጓዳኝም ወጣቶችና ሴቶችን ከዲጂታል ግብርና ጋር እንዲተዋወቁ መሥራት ያስፈልጋልም ብለዋል።            
ባለፉት ሦስት ዓመታት በንግድ ስራ ፈጠራ ሀሳብ ውድድር አሸናፊ የሆኑ 381 ወጣቶች አስተማማኝ የስራ እድል ተፈጥሮላቸዋል- የስራና ክህሎት ሚኒስቴር
Jun 2, 2023 54
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፦ ባለፉት ሶስት ዓመታት "በብሩህ ኢትዮጵያ" የንግድ ስራ ፈጠራ ሀሳብ ውድድር አሸናፊ የሆኑ 381 ወጣቶች ዘላቂ የስራ እድል እንደተፈጠረላቸው የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ንጉሱ ጥላሁን ገለጹ። ለዘንድሮ ውድድር አሸናፊዎች ለእያንዳንዳቸው የስራ ማስጀመሪያ 5 ሺህ ዶላር እንደሚሸለሙ ጠቁመዋል። ሚኒስትር ዴኤታው 4ኛው "ብሩህ ኢትዮጵያ 2015" ብሔራዊ የንግድ ፈጠራ ሃሳብ ውድድር አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ውድድሩ ዘላቂ የስራ ዕድሎችን ለመፍጠር የሚረዳ ሀሳብ ያላቸው ወጣቶች የሚሳተፉበት መድረክ መሆኑን አቶ ንጉሱ ገልጸዋል። "ብሩህ ኢትዮጵያ" የንግድ ሃሳብ ውድድር ከዚህ ቀደም በመንግስት ብቻ ሶስት ጊዜ እንዲሁም ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር ደግሞ አራት ጊዜ በድምሩ ሰባት ጊዜ መካሄዱን አስታውሰዋል። ባለፉት ሶስት ዓመታት በ "ብሩህ ኢትዮጵያ" ፕሮግራም 552 የፈጠራ ሀሳብ ባለቤት ወጣቶች የክህሎት ስልጠና እንዲያገኙ መደረጉን አመልክተዋል፡፡ ከእነዚህ መካከል 167 ምርጥ የንግድ ፈጠራ ሀሳቦች ለውድድር ቀርበው አሸናፊ ለሆኑት ለስራ ማስጀመሪያ የሚሆን የ1 ሚሊዮን 518 ሺህ ዶላር ሽልማት መሰጠቱንን ሚኒስትር ዴኤታው የተናገሩት። በዚህም ባለፉት ሶስት ዓመታት ብቻ በፈጠራ ሃሳብ ውድድር አሸናፊ ለሆኑ 381 ወጣቶች "አስተማማኝ እና ቋሚ የስራ ዕድል መፍጠር ተችሏል" ብለዋል። እንደ አቶ ንጉሱ ገለጻ፤4ኛው "ብሩህ ኢትዮጵያ 2015" ብሔራዊ የንግድ ፈጠራ ሃሳብ ውድድር በሚቀጥለው ወር ይካሄዳል። ከተለያዩ ክልሎች የተመረጡ 200 ተወዳዳሪዎች ከግንቦት 28 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ በቡራዩ የተሰጥኦ ማበልጸጊያ ትምህርት ቤት ገብተው የስራ ፈጠራን የተመለከቱ ስልጠናዎ እንደሚወስዱ አመልክተዋል። ስልጠናውን ከወሰዱት መካከል ለውድድር የሚቀርቡ 70 ባለተሰጥኦዎችን ለመለየት መርሐ-ግብር መዘጋጀቱን አንስተው፤ለ50 አሸናፊዎች ለእያንዳንዳቸው የስራ ማስጀመሪያ 5 ሺህ ዶላር እንደሚሸለሙ ገልጸዋል። የዘንድሮው ውድድር ክልሎችን በስፋት ተደራሽ አድርጓል ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው ይህም በሁሉም አካባቢ ያሉ እምቅ የንግድ ፈጠራ ሀሳቦችን አካታች በሆነ መንገድ ማሳተፍን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።                                                                           መካሔዱን የገለጹት አቶ ንጉሱ      
ኮሪያ ሪፐብሊክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የልማት ትብብር አጠናክራ ትቀጥላለች - አምባሳደር ካንግ ሶኪ
Jun 2, 2023 41
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፦ ኮሪያ ሪፐብሊክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የልማት ትብብር አጠናክራ እንደምትቀጥል በኢትዮጵያ የአገሪቱ አምባሳደር ካንግ ሶኪ ገለጹ። አምባሳደር ካንግ ለኢዜአ እንደገለጹት ኮሪያ ሪፐብሊክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ዲፕሎማሲያዊ በተለይም በልማት መስኮች ያላቸውን ትብብር እየተጠናከረ መምጣቱንና ይህንንም ይበልጥ ለማጠናከር እየተሰራ ነው ብለዋል። የሰላም ስምምነቱን ተከትሎ ኮሪያ ሪፐብሊክ በሰሜን የኢትዮጵያ ክፍል ያላትን የልማት ፕሮጀክቶች መልሶ ለማስጀመር የሚያስችሉ ዝግጅቶች እያደረገች መሆኑን አመልክተዋል። የኮሪያ ሪፐብሊክ መንግስት ቀደም ሲል ለኢትዮጵያ 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ዶላር የሰብዓዊ ድጋፍ 10 ሚሊየን ዶላር ግምት ያለው የምግብ ድጋፍ ማድረጉን ተናግረዋል። በቀጣይም ተጨማሪ የሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረግና የተቋረጡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን ስራ ለማስጀመር እንቅስቃሴ መጀመሩን ነው አምባሳደር ካንግ የጠቀሱት። ለሰላም ስምምነቱ ተግባራዊነት የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ ትቀጥላለች ብለዋል። በቀጣይም የኮሪያ ሪፐብሊክ መንግስት በምስራቅ አፍሪካ ለኢትዮጵያ፣ ኬንያ እና ሶማሊያ ከ8 ሚሊዮን ዶላር በላይ የምግብ እና ሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረግ ማቀዱን ጠቁመዋል።   የኢትዮጵያና ኮሪያ ሪፐብሊክ ወዳጅነት የተጀመረው እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1950ዎቹ ሲሆን ይፋዊ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የተጀመረው እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር 1963 ነው።            
በአማራ ክልል ባለፉት 10 ወራት ከ960 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ተፈጥሯል-የክልሉ ስራና ስልጠና ቢሮ
Jun 2, 2023 32
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በተያዘው በጀት ዓመት 10 ወራት ከ960 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፍጠሩን የክልሉ ስራና ስልጠና ቢሮ አስታወቀ። የአማራ ክልል ስራና ስልጠና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ አወቀ ዘመነ ለኢዜአ እንደገለጹት በአማራ ክልል አሁን ላይ ያለው የስራ አጥነት ምጣኔ 19 ነጥብ 1 በመቶ ይጠጋል። በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል የነበረው ጦርነት በክልሉ በሚገኙ ሃብቶች ላይ ያደረሰው መጠነ ሰፊ ውድመት የስራ ፈላጊው ቁጥር እንዲያሸቅብ ማድረጉንም ተናግረዋል፡፡ ይህን ከግምት ውስጥ በማስገባት በተያዘው በጀት ዓመት ለስራ ዕድል ፈጠራ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ ወደ ስራ መግባቱን ገልጸዋል። በዚህም በ2015 ዓም በጀት ዓመት 1 ሚሊዮን 203 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ ዕድል ለመፍጠር ዕቅድ ተይዞ ወደ ስራ መገባቱን አስታውሰዋል። ይህን ተከትሎ በበጀት ዓመቱ በተሰራው ስራ ባለፉት 10 ወራት ለ 967 ሺህ 584 ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ጠቅሰዋል። አፈጻጸሙ በዓመቱ ከተያዘው እቅድ ውስጥ 80 በመቶውን ያሳካ መሆኑን ነው የገለጹት። ከዚህ ውስጥ ለ647 ሺህ 520 ዜጎች ቋሚ የስራ ዕድል የተፈጠረላቸው ሲሆን ቀሪዎቹ ጊዜያዊ የስራ ዕድል ያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ በአብዛኛው የተፈጠረው የስራ ዕድል በግብርና፣ በኢንዱስትሪ እና በአገልግሎት ዘርፍ መሆኑን ጠቅሰዋል። ክልሉ በበጀት ዓመቱ ለስራ ዕድል ፈጠራ 3 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር መደበኛና ተዘዋዋሪ ብድር ለመስጠት አቅዶ 2 ነጥብ 99 ቢሊዮን ብር ብድር መስጠት መቻሉን ነው የጠቀሱት። በቀሪዎቹ ሁለት ወራት ተጨማሪ የስራ ዕድል እንደሚፈጠርና አሁን ላይ በክልሉ በስራ ዕድል ፈጠራ በኩል መልካም አፈጻጻም መመዝገቡን ነው የገለጹት። ባለፈው በጀት ዓመት በክልሉ በአጠቃላይ የተፈጠረው የስራ ዕድል 965 ሺ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ በዚህ ዓመት ቀሪዎቹን ወራቶች ሳይጨምር በ10 ወር ብቻ የተፈጠረው የስራ ዕድል ከቀደመው ዓመት የላቀ መሆኑን በስኬት አንስተዋል። በቀጣይ ከዚህ በፊት በስራ ዕድል ፈጠራ ዙሪያ ይታይ የነበረውን የተቋማት የቅንጅት ችግር ለመፍታት በርዕሰ መስተዳደሩ የሚመራ የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት ምክር ቤት ማቋቋሚያ ደንብ ጸድቆ ወደ ታችኛው መዋቅር እንዲወርድ ተደርጓል ነው ያሉት።  
የሰው ሰራሽ ማዳበሪያ እጥረትን ለማቃለል ያዘጋጀነውን የተፈጥሮ ማዳበሪያ ተጠቅመን ወደዘር ሥራ ገብተናል- የሰሜን ወሎ ዞን አርሶ አደሮች
Jun 2, 2023 43
ወልዲያ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፡- የሰው ሰራሽ ማዳበሪያ እጥረትን ለማቃለል በበጋው ያዘጋጁትን 6 ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ የተፈጥሮ ማዳበሪያ በመጠቀም ቀድመው የሚዘሩ ሰብሎችን እየዘሩ መሆኑን የሰሜን ወሎ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ ጉባላፍቶ ወረዳ የአላውሃ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ብርሃን ጎበና ለኢዜኣ እንደገለጹት በበጋ ወቅት 51 ሜትር ኪዩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘጋጅተዋል። እሳቸውን ጨምሮ የቀበሌያቸው አርሶ አደሮች ሰው ሰራሽ ማዳበሪያ እንዲቀርብላቸው የሚመለከታቸው የአስተዳዳር አካላትን ቢጠይቁም "ይመጣል" ከሚል ውጭ እስካሁን ማዳበሪያ እንዳላገኙ ተናግረዋል። በእዚህም ቀድሞ ለሚዘራው ማሽላ ሰው ሰራሽ ማዳበሪያው እንዳልደረሰላቸው ገልጸው፣ በእዚህም በበጋው ያዘጋጁትን የተፈጥሮ ማዳበሪያ በማሳቸው ላይ ቀድመው በመበተን ማዋሀዳቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም ማሽላ ለመዝራት መቻላቸውን ነው የገለጹት። "ሰው ሰራሽ ማዳበሪያው ቀድሞ ለተዘራው ማሽላ ባይደርስም በመጪው ሰኔ ወር ለሚከናወነው የዘር ሥራ የሚመለከተው አካል ፈጣን መፍትሄ ይስጠን" ሲሉ ጠይቀዋል። በራያና ቆቦ ወረዳ የወርቄ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ከተማ አበጋዝ በጓሯቸው በበጋው ወቅት ያዘጋጁትን 51 ሜትር ኪዩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማሳቸው ላይ ላይ በመበተንና በማዋሃድ ማሽላ መዝራታቸውንም ተናግረዋል። ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ የህልውና ጉዳይ በመሆኑ ከመጪው ሰኔ ወር አጋማሽ ጀምሮ ለሚዘሩት ጤፍ፣ ስንዴና ሌሎች ሰብሎች ዘር ፈጥኖ እንዲቀርብላቸው ጠይቀዋል። ከሰብልና ከእንስሳት ተረፈ ምርትና ከአካባቢ ግብአት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማዘጋጀታቸውን የገለጹት አቶ ከተማ፣ "ይህም ለማዳበሪያ የሚያወጡትን ወጭ ከማስቀረት ባለፈ የማዳበሪያ እጥረት ችግሩን ለመሻገር ያስችላል" ብለዋል። በሰሜን ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ የግብዓት አቅርቦት ቡድን መሪ አቶ ፀጋ ውቤ በበኩላቸው፣ ለ2015/16 የመኽር እርሻ ከሚያስፈልገን 153ሺህ ኩንታል ሰው ሰራሽ ማዳበሪያ እስካሁን ወደዞኑ የገባው 24ሺህ ኩንታል ብቻ ነው። "ቀሪው ማዳበሪያ ወደብ ላይ መድረሱንና በመጓጓዝ ላይ ስለመሆኑ በሚመለከተው አካል ተገልጾልናል" ያሉት አቶ ጸጋ፣ ማዳበሪያው እንደደረሰ በፍትሀዊነት ለአርሶ አደሩ እንደሚሰራጭ አመልክተዋል። አርሶ አደሮቹን በመደገፍ ከ5 ነጥብ 9 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ በማዘጋጀት 3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ የሚሆነውን ቀደሞ ለሚዘሩ ሰብሎች ጥቅም ላይ መዋሉን ገልጸዋል። በተጨማሪም 23ሺህ 320 ሜትር ኪዩብ የባዮ ጋዝ ሰለሪ፣ ከ9ሺህ ኩንታል በላይ የቨርሚን ኮምፖስት ተዘጋጅቶ ጥቅም ላይ የዋለ ሲሆን፣ ይሄም ለአፈር ለምነትና ለምርታማነት ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን አስረድተዋል። ጥራጥሬና ጤፍ የሚዘራበት የክረምት ወቅት ሳያልፍ ለዞኑ የሚያስፈለገውን ሰው ሰራሽ ማደበሪያ ለማቅረብ ከሚመለከታቸው ጋር በመነጋገር ላይ መሆናቸውንም አቶ ጸጋ አስታውቀዋል። በሰሜን ወሎ ዞን ለ2015/16 የምርት ዘመን 231ሺህ 578 ሄክታር መሬት በዘር በመሸፈን ከ6 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ ከዞኑ ግብርና መምሪያ የተገኘ መረጃ ያመላክታል።    
የጭሮ ከተማ በልዩ የስራ እድል ፈጠራ ፕሮግራም ከ1ሺህ 400 በላይ ወጣቶችን የእድሉ ተጠቃሚ ለማድረግ እየሰራ ነው
Jun 2, 2023 41
ጭሮ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ):-በጭሮ ከተማ ከ1 ሺህ 400 በላይ ወጣቶችን በልዩ ስራ እድል ፈጠራ ፕሮግራም በጎጆ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለማሰማራት እየሰራ መሆኑን የከተማው ስራ እድል ፈጠራና ክህሎት ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ የጭሮ ከተማ ስራ እድል ፈጠራና ክህሎት ጽህፈት ቤት ከባለድርሻ አካላት ጋር መክሯል። በውይይቱም ለወጣቶቹ ልዩ የስራ ፈጠራ ፕሮግራም እየተመቻቸ መሆኑ ተገልጾ፤ በዚህም በጎጆ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለ1ሺህ 412 ስራ አጥ የከተማው ወጣቶች የመስሪያ ቦታዎችንና የስራ ማስኬጃ የገንዘብ ብድር ለማመቻቸት ትግበራው መጀመሩ ተገልጿል፡፡ የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ ወይዘሮ ዘሃራ ኢብራሂም በዚሁ ጊዜ እንዳብራሩት የ2015 በጀት ሳይጠናቀቅ በሚተገበረው ስራ ለ1 ሺ 412 የከተማው ስራ አጥ ወጣቶች እድሉን ለማመቻቸት እየሰራ ነው።   ስራው በበላይነት የሚከናወነውም በባድርሻ አካላቱ ትብብር አማካይነት መሆኑን አክለዋል፡፡ ይህን ስራ ተግባራዊ ለማድረግም ወጣቶቹን በ282 ማህበራት በማደራጀት የስራ እድሉ የሚሰራ ሆኖ ለዚህም 7 ሚሊዮን ብር ስራ ማስጀመሪያና 2 ነጥብ 5 ሔክታር መሬት ለመስሪያ ቦታ እንደሚሰጥ ገልፀዋል፡፡ ስራ አጥ ወጣቶቹ እንዲሰማሩበት የተፈለገው የጎጆ ኢንዱስትሪ ዘርፍም የሸክላ ስራ፣ የቆዳ ውጤቶች ስራ፤ ልብስ ስፌትና ሽመና መሆናቸውንም ኃላፊዋ አያይዘው ገልፀዋል፡፡ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በሚፈለገው አግባብ ሁሉንም ስራዎች ውጤታማ ለማድረግ የበኩላቸውን እንዲወጡም አሳስበዋል፡፡ ከውይይቱ ተሳታፊ ባለድርሻ አካላት መካከል የጭሮ ከተማ ማዘጋጃ ቤት ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ አመዲን ኢብሮ የከተማችንን ወጣቶች በጎጆ ኢንዱስትሪ ስራዎች ላይ በማሳተፍ የከተማችንን ገጽታ መለወጥ የምንችልበት እድል መፍጠር ነው ብለዋል፡፡   ከተማዋ ባላት አቅም ልክ ወጣቶቹ ስራ ፈጥረው ተጠቃሚ የሚሆኑበትን እድል በማመቻቸት ሰላሟ የተረጋገጠ ከተማን ከመፍጠር ባሻገር ውብና ማራኪ ገፅታን ማላበስ እንደሚቻልም አክለዋል፡፡ የንግድ ስራ ማህበራትን ማሳተፍ ለስራው መፋጠን ትልቅ ጥቅም እንዳለው ጠቁመው በታቀደው ጊዜ ተጠናቆ ለተጠቃሚዎች መድረስ እንዳለበትም ተናግረዋል፡፡ ሌላዋ ተሳታፊ የጭሮ ከተማ ሰራተኛና ማህበራዊ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ፋሲካ እሸቱ የስራ አጥ ቁጥሩን ለመቀነስ የሚደረገውን ጥረት ለማሳካት ችግሩን ከስሩ ከማጥናት መጀመር እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡ ስራ አጥ ወጣቶች ተቀማጭ ገንዘብ የሌላቸው መሆኑን ያገናዘበ የብድር አገልግሎት በመስጠት ለስራው ውጤታማነትና ስኬት ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባም አክለዋል፡፡ እንደ ወይዘሮ ፋሲካ ገለጻ በተለይ ባንኮች ለስራ አጦች ልዩ የብድር አገልግሎት በማመቻቸት ቢተባበሩ በገንዘብ እጥረት ምክንያት የሚፈጠረውን ችግር መቅረፍ እንደሚቻል ገልፀዋል፡፡    
በምዕራብ ወለጋ ዞን የሩዝ ምርትን በዞኑ ምቹ ስነ ምህዳር ባላቸው ወረዳዎች ለማስፋት እየተሰራ ነው - የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት
Jun 2, 2023 44
ጊምቢ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ):- በምዕራብ ወለጋ ዞን በሙከራ ደረጃ የነበረውን የሩዝ ምርት በዞኑ ምቹ ስነ ምህዳር ባላቸው ወረዳዎች ለማስፋት እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በዞኑ ከ112 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በሩዝ ምርቱ ላይ እየተሳተፉ እንደሚገኝ ገልጿል። ከዚህ ቀደም በምዕራብ ወለጋ ዞን የነበሩ አርሶ አደሮች ኑሮ በቡና ምርት ላይ ብቻ የተወሰነ ነበር። ይሁንና የሩዝ ምርት በማይታወቅበት ዞን ላለፈው ሁለት ዓመት በገንጂ ወረዳ የሩዝ ምርት በሙከራ (ፓይለት) ደረጃ ሲመረት ቆይቷል። የዞኑ የግብርና ጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ፈይሳ ሀምቢሳ እንደገለጹት በግብርና ባለሙያዎች እገዛ የሩዝ ምርት እየተለመደ መምጣቱን እና ምርቱ በክልሉ መንግስት ትኩረት ከተሰጣቸው ኢንሼቲቮች መካከል እንደሚገኝበት ገልጸዋል። በዚህም በዞኑ ለሩዝ ምርት አመቺ በሆኑ ወረዳዎች ምርቱን ለማስፋት እየተሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል።   በዘንድሮ ዓመት 88 ሺህ 127 ሔክታር መሬት በላይ በሩዝ ምርት በመሸፈን ከ3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሩዝ ምርት ለማምረት መታቀዱን ጠቁመዋል። እስካሁን በተከናወነው ስራ ከ2 ሺህ 205 ሔክታር መሬት በላይ በዘር ለመሸፈን መቻሉን ነው አቶ ፈይሳ የተናገሩት። ለዚህም የሚያስፈልጋቸው የአፈር ማዳበሪያ ከ100 ሺህ ኩንታል በላይ ለአርሶ አደሩ ቀርቦ እንደሚሰራጭ ገልጸዋል። በምዕራብ ወለጋ ዞን ከ112 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በሩዝ ምርቱ ላይ እየተሳተፉ መሆናቸውን አመልክተዋል። የኦሮሚያ ክልል መንግስት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የአርሶ አደሩን ኑሮ ለማሻሻል እንዲሁም ምርትና ምርታማነት ለመጨመር የተለያዩ የግብርና ኢንሺቲቮችን ቀርጾ በስራ ላይ ማዋሉን ተናግረዋል። በግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች የአርሶ አደሮችን አመለካከት በመቀየር ሩዝ በዓመት ሁለትና ከዚያ በላይ በማምረት ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የበጋ መስኖና ሌሎች ገበያ ተኮር ሰብሎች እንዲያመርቱ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በሩዝ ምርቱ ላይ ተሳታፊ የሆኑ አርሶ አደሮች በበኩላቸው ከሁለት ዓመት በፊት በበጋ መስኖ ስንዴ በማምረት ተጠቃሚ መሆናቸውን አስታውሰው አሁን ላይ በሩዝ ምርት ላይ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በባለሙያ እገዛ እያመረቱ መሆኑን ገልጸዋል። የባለሙያን ምክር በአግባቡ በመጠቀም የተሻለ ምርት ለማግኘት በትኩረት እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።  
በኦሮሚያ ክልል በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ  ከ120 በላይ ኢንዱስትሪዎች ዳግም ወደ  ስራ ገብተዋል - የክልሉ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ቢሮ
Jun 2, 2023 43
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ ምክንያቶች ስራ አቁመው የነበሩ ከ120 በላይ ኢንዱስትሪዎች በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ዳግም ወደ ስራ መግባታቸውን የኦሮሚያ ክልል ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ገለጸ፡፡ እንደ አገር የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከተጀመረ አንድ ዓመት ወዲህ በርካታ ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ መግባታቸው የሚታወቅ ሲሆን ሌሎች ስራ አቁመው የነበሩ ኢንዱስትሪዎችም ዳግም ወደ ስራ ተመልሰዋል፡፡ በንቅናቄው ለኢንዱስትሪዎችና ኢንተርፕራይዞች የተቀናጀ የአቅም ግንባታ፣ የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት ድጋፍ ተድርጎ የማምረት አቅማቸው ከፍ እያለ መምጣቱም ይታወቃል፡፡ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በተለይ በጨርቃ ጨርቅ፣ በምግብና ምግብ ነክ፣ በማኑፋክቸሪንግና ኢንዱስትሪ ምርቶች ዘርፈ ብዙ ውጤቶች መመዝገባቸውንም እንዲሁ፡፡ የኦሮሚያ ክልል ኢንቨስትመንት እና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ አቶ አህመድ እድሪስ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ንቅናቄው በክልሉ ለሚገኙ ኢንዱስትሪዎች መነቃቃት ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ንቅናቄው ተግባራዊ ከተደረገ ወዲህ ኢንዱስትሪዎች ከፍተኛ ምርት እንዳያመርቱ ማነቆ የሆኑባቸው ችግሮች ተለይተው መፈታታቸውን ጠቁመዋል፡፡ በክልሉ ስራ አቁመው የነበሩ ከ120 በላይ ኢንዱስትሪዎች የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከተጀመረ ወዲህ ዳግም ወደ ስራ መግባታቸውን ተናግረዋል፡፡ ስራ የገቡት ኢንዱስትሪዎችም ከፍተኛ፣ መካከለኛ እና አነስተኛ የሚባሉ ስለመሆናቸውም በመጠቆም፡፡ በተጨማሪም በቅንጅት በተሰራው ስራ ከ2 ሺ በላይ ፕሮጀክቶች ወደ ግንባታ እንዲገቡ መደረጉንም ጠቁመዋል፡፡ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ የሚገኙ ኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም ከፍ ማድረጉን ጠቁመው፤ 41 በመቶ የነበረውን አማካኝ የማምረት አቅም ወደ 51 ከፍ ማድረጉን ጠቁመዋል፡፡ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በአገር አቀፍ ደረጃ ሚያዚያ 29 ቀን 2014 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ይፋ መደረጉ ይታወቃል።    
በሀገር አቀፍ ደረጃ አንድ ወጥ የግብርና መረጃ ቋት እየተዘጋጀ ነው - የግብርና ሚኒስቴር
Jun 2, 2023 55
አዳማ ኢዜአ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ):- የግብርና ሚኒስቴር በአገር አቀፍ ደረጃ አንድ ወጥ የሆነ ዘመናዊ የግብርና መረጃ ስርዓት ለመዘርጋት የሚያስችል የመረጃ ቋት እየተዘጋጀ እንደሚገኝ አስታወቀ። የግብርና መረጃ የባለድርሻ አካላት አውደ ጥናት በአዳማ ከተማ እየተካሄደ ነው። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ፍቅሩ ረጋሳ እንደገለጹት በግብርናው ላይ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችን ጥራት ባለው ወቅታዊ መረጃ መደገፍ ይገባል። በሚኒስቴሩ በእንስሳት እና ዓሳ ዘርፍ ብቻ ስምንት የመረጃ ቋት መኖራቸውንና በአሁኑ ወቅት በተለያዩ ዘርፎች ተበታትነው ያሉትን ወደ አንድ በማምጣት ዲጂታል የሆነ አገራዊ የመረጃ ቋት የማዘጋጀት ስራ እየተከናወነ ነው ብለዋል።   አገራዊ የሆነ አንድ የመረጃ ቋት መገንባት የመረጃ ድግግሞሽና የመረጃ ጥራት በማስጠበቅ ኢትዮጵያ የዲጂታል የመረጃ ስርዓት ማዕከል እንዲኖራት የሚያስችል እንዲሁም ወጪ ቆጣቢ በመሆን የእውቀት፣ የጉልበት እና ሀብት ብክነትን የሚያስቀር መሆኑን አመልክተዋል። የሚገነባው አገራዊ የመረጃ ቋት በቅንጅት መረጃ ለመሰብሰብ፣ ለማጋራት እና ለመጠቀም እንደሚያስችልም ተናግረዋል። የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ማንደፍሮ ንጉሴ በበኩላቸው መረጃ አሁን ያለውን የግብርና ስርዓት ለመለወጥ እና ለማዘመን ዲጂታል የሆነ የመረጃ አሰባሰብና አጠቃቀም ወሳኝ ነው ብለዋል።   ባለድርሻ አካላት አንድ አገራዊ የመረጃ ቋት እንዲገነባ የበኩላቸውን ድጋፍ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው አመልክተዋል። በአውደ ጥናቱ ላይ የግብርና ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢኒስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስ እና ጂኦ-ስፓሻል ኢንስቲትዩት፣ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት እና የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በመረጃ አሰባሰብና ዲጂታላይዜሽን በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። የግብርና መረጃን የባለድርሻ አካላት አውደ ጥናት እስከ ነገ ይቆያል።
በቤንች ሸኮ ዞን የድልድይ መሠረተ ልማቶች በኅብረተሰብ ተሳትፎ እየተሰሩ ነው
Jun 2, 2023 34
ሚዛን አማን፤ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፡-በዞኑ በተለያዩ ወረዳዎች ውስጥ የሚታየውን የድልድይ መሠረተ ልማት ችግር በኅብረተሰብ ተሳትፎ ለመፍታት የተጀመረው ጥረት ውጤት እያስገኘ መሆኑን የቤንች ሸኮ ዞን አስተዳደር አስታወቀ። በዞኑ ለረጅም ጊዜያት ጥያቄ ሆነው የቆዩ የድልድይ መሰረተ ልማት ችግሮችን ለመፍታት ህብረተሰቡን በማቀናጀትና በማሳተፍ የተጀመረው ስራ ተሞክሮ የሚሆን ነው የተባለው። የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ እና የፋይናንስ መምሪያ ኃላፊ አቶ ሳሙኤል አሰፋ እንዳሉት በዞኑ የድልድይ መሰረተ ልማት ችግር በስፋት ይታያል። ይህም አርሶ አደሮች ምርቶቻቸውን በአግባቡ ገበያና በማውጣት የሚጠበቀውን ጥቅም እንዳያገኙ ከመከልከል ባለፈ ለሌሎችም ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ የልማት እንቅስቃሴዎች ተግዳሮት መሆኑን ተናግረዋል። የአካባቢው ኅብረተሰብ የቅሬታ ምንጭ ከነበሩ የመሠረተ ልማት ጉድለቶች ውስጥ የመንገድና ድልድይ ችግር ቀዳሚ ሲሆን የሚያመርቱትን የግብርና ውጤት ለገበያ ለማውጣት እንደሚቸገሩ ተናግረዋል። ችግሩን ለመፍታት አስተዳደሩ በየአከባቢው የማህበረሰብ ተሳትፎን በማጠናከርና በማቀናጀት ስራ መጀመሩን ገልጸው፤ ይህም ተሞክሮ የሚሆን ውጤት እየተገኘበት መሆኑን አስረድተዋል። ለአብነትም ችግሩ ከሚታይባቸው ወረዳዎች መካከል የደቡብ ቤንች ሼይ ቤንችና ሸኮ ወረዳዎች በህብረተሰብ ተሳትፎ ብቻ የአምስት ድልድዮች ግንባታ ተጀምሮ ሶስቱ ተጠናቅቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን ገልጸዋል። ከፍተኛ የሆነ የድልድይ መሰረተ ልማት ችግር ከነበረባቸው አንዱ የሆነው የደቡብ ቤንች ወረዳ በሁለት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ሦስት በኅብረተሰብ ተሳትፎ የተገነቡ ድልድዮችን ማስመረቅ መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም የቡና፣ ኮረሪማና ሙዝ እንዲሁም ሌሎች የግብርና ምርቶችን ለወረዳ፣ ለዞን እና ለማዕከላዊ ገበያ የሚያልፍበት የሾር ወንዝ ድልድይ ግንባታ ተጠቃሽ ሲሆን በዚህ ወንዝ ላይ ድልድይ መገንባቱ አሁን ላይ በአካባቢው ከፍተኛ የኢኮኖሚ መነቃቃት መፍጠር ችሏል ነው ያሉት። ይህንን ተሞክሮ በሌሎች ወረዳዎች በማስፋፋት የድልድይ ግንባታ እጥረት እያስነሳ ያለውን ጥያቄ በኅብረተሰብ ተሳትፎ ለመመለስ እየተሰራ ነው ያሉት አቶ ሳሙኤል፤ በሼይ ቤንችና ሸኮ ወረዳ ሂደት ላይ የሚገኙ ሁለት ፕሮጀክቶች ግንባታ መጀመራቸውን ጠቅሰዋል። የደቡብ ቤንች ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ወልዱ ባቺ በበኩላቸው የአካባቢው ኅብረተሰብ ለፌች፣ ሾር እና ዘልሚ ወንዞች ድልድይ ግንባታ ከ25 ሚሊዮን ብር በላይ በማዋጣት ሙሉ ወጪ መሸፈኑን ገልጸዋል። በኅብረተሰብ ተሳትፎ የተገነቡ እነዚህ ሦስት ድልድዮች ከ12 በላይ ቀበሌዎችን እርስ በእርስ እና ከወረዳው ጋር እንዲሁም ከዋናው የዞን መንገድ ጋር ማገናኘት እንደሚችሉም ጠቅሰዋል። ድልድዮቹ የህዝባችንን ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ችግር የሚቀርፉ ሲሆን ለአብነትም የሾር ወንዝ ድልድይ ከተመረቀ በኋላ ከ10 በላይ በቡና ኢንዱስትሪ የተሰማሩ ባለ ሀብቶች ወንዙን ተሻግረው ሥራ መጀመራቸውን ጠቁመዋል። የመንግስትን እጅ በመጠበቅ ፈጣን የመሠረተ ልማት ዝርጋታን ማሟላት ስለማይቻል በመተባበር ልማቶችን በራስ አቅም ከፍ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አመላክተዋል። በወረዳው በማኅበረሰብ ሙሉ ወጪ የተገነባው ሦስተኛ የዘልሚ ወንዝ ድልድይ ትናንት የተመረቀ ሲሆን አምስት ቀበሌዎችን ከወረዳው ጋር የሚያገናኝ ነው ብለዋል። ከአካባቢው ነዋሪዎች መካከል የዞዞ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አዳሙ ጃርሹ በዘልሚ ወንዝ ምክንያት "ከዚህ ቀደም የምናመርተውን ቡና፣ ሙዝና ሌሎች የግብርና ምርቶችን ወደ ገበያ ለማቅረብ እንቸገር ነበር" ብለዋል። ከወረዳው 11 ኪሎ ሜትር ያህል ርቀት ላይ በሚገኘው የዘልሚ ወንዝ ምክንያት ወላድ እናቶችን ወደ ጤና ተቋም በአምቡላንስም ሆነ በሌላ ተሽከርካሪ ማድረስ የማይቻል እንደሆነ አስታውሰው፤ አሁን ላይ በድልድዩ መገንባት ችግሩ መቀረፉን ገልጸዋል። ለድልድዩ ግንባታ የአካባቢያቸውን ማኅበረሰብ በማስተባበር የድጋፍ ገቢ የማሰብሰብ ሥራ ሲሰሩ እንደነበርም ነው የተናገሩት። ሌላው የአካባቢው ነዋሪ አቶ ማርቆስ ከበደ በበኩላቸው በክረምት ወቅት በሚፈጠረው የውሃ ሙላት ምክንያት ወንዙን ተሻግሮ መገበያየትና ማኅበራዊ ግንኙነት መፍጠር እንደማይቻል ተናግረዋል። ከግንኙነት መፍጠር ባሻገር ምርታቸውን በአግባቡ ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለመሆን የሚያስችል ዕድል በራሳችን አቅም ፈጥረን በማስመረቃችን ደስተኞች ነን ሲሉም ተናግረዋል። በወረዳው በማኅበረሰብ ድጋፍ እየተሰሩ ያሉ የድልድይ ሥራዎችን ተከትሎ በተፈጠረው መነሳሳት ከ30 ኪሎ ሜትር በላይ አዲስ የጥርጊያ መንገድ በዞኑ አስተዳደር መሰራቱም ተመላክቷል።    
በንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እጥረት ለተጨማሪ ወጪና እንግልት እየተዳረግን ነው -- በደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪዎች
Jun 2, 2023 45
ደብረ ብርሀን ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፡-በደብረ ብርሀን ከተማ በንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት እጥረት ለተጨማሪ ወጪና እንግልት እየተዳረጉ መሆናቸውን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ የውሃና ፍሳሽ አገልግሎት በበኩሉ ህብረተሰቡ ያነሳው ጥያቄ ትክክል መሆኑን አምኖ ችግሩን ለመፍታት እየተሰራ መሆኑን አስታውቋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ነዋሪዎች መካከል በደብረ ብርሃነ ከተማ ቀበሌ 06 የሚኖሩት አቶ አበጋዝ ገስጥ እንዳሉት፣ በሚኖሩበት ኡራኤል ሰፈር የመጠጥ ውሃ አስከ 20 ቀን ሳያገኙ የሚጠፋበት ጊዜ አለ። በዚህም በቀን 20 ሊትር በሚይዝ ጀሪካን ከሌላ አካባቢ አስቀድቶ ለማስመጣት ከነማጓጓዣው አስከ 60 ብር በማውጣት ለወጪና እንግልት እየተዳረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ውሃ ለመቅዳት ከአካባቢያቸው ርቀው ሲሄዱ ሌሊት እንደሚነሱ የገለጹት አቶ አበጋዝ፣ ለውሃ የሚባክነው ጊዜም በመደበኛ ሥራቸው ላይ ጫና እንዳሳደረባቸው ገልጸዋል። "የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እጥረት ለተጨማሪ ወጪና እንግልት ከመዳረግ በላይ ከወንዝ የምንቀዳው ውሃ የጤናም ስጋት በመሆኑ ከተማ አስተዳደሩ አፋጣኝ ምላሽ ሊሰጠን ይገባል" ሲሉም ጠይቀዋል።   በከተማው የቀበሌ 07 ነዋሪ አቶ ውብሸት መንግስቱ በበኩላቸው ውሃ ከሌላ ቦታ ገዝተው ለማስመጣት የሚከፍሉት ገንዘብ ካለው የኑሮ ውድነት ጋር ተያይዞ ተጨማሪ ጫና እየፈጠረባቸው መሆኑን ገልጸዋል። ከወንዝና ከጉድጓድ ተቀድቶ የሚመጣ ውሃ የተበከለ በመሆኑ በእሳቸውና በቤተሰባቸው ጤና ላይ ችግር እየፈጠረ መሆኑን የገለጹት ነዋሪው፣ "በእዚህም ለህክምና ወጪ እየተዳረግን በመሆኑ የሚመለከተው አካል ፈጣን ምላሽ ይስጠን" ሲሉ ጠይቀዋል።   የደብረ ብርሀን ከተማ ውሃና ፍሳሽ አገልግሎት ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ እንደውቀቱ መታፈሪያ ስለ ጉዳዩ ተጠየቀው በሰጡት ምላሽ፣ በአንዳንድ የከተማዋ አካባቢዎች የንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ችግር መኖሩን አምነዋል። በከተማዋ የተፈናቃዮች ቁጥር መጨመር፣ በተዘረጉ የውሃ መስመሮች ላይ የሚደርስ ጉዳት፣ የግንባታ ሥራዎች መስፋፋትና በውሃ መስመሮችና ቆጣሪዎች ላይ የሚደርስ ዝርፊያ ችግሩ እንዲባባስ አስተዋጽኦ ማድረጉን ገልጸዋል። ከተማ አስተዳደሩ ችግሩን ለመፍታት እየሰራ መሆኑን ያመለከቱት ሥራ አስኪያጁ፣ "የከተማዋን የውሃ አቅርቦት አቅም የሚያሳድግ የውሃ ማጠራቀሚያ ጋን ግንባታና የውሃ መስመር ዝርጋታ ሥራዎች በ75 ሚሊዮን ብር እየተከናወኑ ይገኛሉ" ብለዋል። በተጨማሪም ሦስት ጥልቅ የውሃ ጉድጓዶች ቁፋሮ ሥራን በከተማ አስተዳደሩና በኢትዮጵያ ውሃ ቴክኖሎጂ የገንዘብ ድጋፍ ለማስጀመር እንቅስቃሴ ላይ መሆኑን ነው የገለጹት። በከባድ የውሃ መስመር ላይ ባሉ የውሃ ቆጣሪዎችና ሌሎች መሳሪያዎች ላይ የሚፈጸምን ዝርፊያ ለመከላከልም ችግሩ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ከህብረተሰቡ ጋር በመወያየትና ኮሜቴ በማዋቀር ለንብረቶች ጥበቃ እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል። የከተማዋን የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ችግር በጥናት በመለየት የከተማዋን ዕድገት መሰረት ያደረገ ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠትም ህብረተሰቡን ያሳተፈ ኮሚቴ ተቋቁሞ ወደ ተግባር መግባቱን ምክትል ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በተያዘው ዓመት ከሱዳንና ከሶማሊያ የመጡትን ጨምሮ ከ110 ሺህ በላይ ስደተኞችን ተቀብላለች- የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት
Jun 2, 2023 75
አዲስ አበባ ግንቦት 25 /2015 (ኢዜአ) ኢትዮጵያ በተያዘው ዓመት ሱዳንና ሶማሊያን ጨምሮ ከተለያዩ ሀገራት ከለላ ፈልገው የመጡ ከ110 ሺህ በላይ ስደተኞችን መቀበሏን የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት አስታወቀ። ለስደተኞች የተሟላ አገልግሎት ለማቅረብ በመተማ እና በኩምሩክ አዲስ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ግንባታ መጀመሩን አገልግሎቱ አስታውቋል።   የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሙሉዓለም ደስታ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ ወደ ግዛቷ የሚገቡ ስደተኞችን ከለላ በመስጠት የምትታወቅበትን ታሪክ በማስቀጠል በዚህ ወቅት ከአንድ ሚሊዮን በላይ የውጭ ሀገራት ዜጎችን አስጠልላ እንደምትገኝ ተናግረዋል። በዚህ ዓመት ብቻ እስካሁን ከ110 ሺህ በላይ ስደተኞችን ከሶማሊያ እና ከሱዳን በግጭት የተፈናቀሉ ዜጎችን ተቀብላ በዓለም አቀፍ መርህ መሰረት አስፈላጊውን ሰብዓዊ ድጋፍ እያቀረበች መሆኗን ነው የተናገሩት። በተለይም የሱዳንን ግጭት ተከትሎ በአማራ ክልል መተማ፣ በቤንሻንጉል ጉሙዝ ኩምሩክ እና በጋምቤላ በኩል በመቀበል ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። እስካሁን በመተማ ብቻ ከ30 ሺህ በላይ ስደተኞች መካከል የጥገኝነትና የከለላ ጥያቄ ያቀረቡ 6 ሺህ 483 የውጭ ዜጎች ምዝገባ መከናወኑን አብራርተዋል። ስደተኞችን የተሟላ አገልግሎት ለማቅረብ በመተማ እና በኩምሩክ የመጠለያ ጣቢያ ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመሩን ገልፀው፤ በመተማ 57 ሄክታር በኩምሩክ አራት ሄክታር መሬት ከክልሎች መረከቡን ገልጸዋል። በግጭት ምክንያት ከሶማሊያ ለመጡ የውጭ ዜጎች በሶማሌ ክልል ዶሎ ዞን ቦኦ ወረዳ ሚርቃን ቀበሌ ክልሉ ባመቻቸው 400 ሄክታር መሬት ላይ አዲስ መጠለያ በመገንባት እስካሁን ከ20 ሺህ በላይ የሚሆኑ ስደተኞች ወደ መጠለያው መግባታቸውን ተናግረዋል። የተመድ የረድኤት ድርጅቶችን ጨምሮ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ስደተኞችን በመደገፍ በጎ አስተዋፅኦ ቢያደርጉም በሚጠበቀው ልክ ባለመሆኑ ይበልጥ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ጠይቀዋል። ስደተኞችን የመቀበልና የማስተናገድ ተግባር ከፀጥታና ደህንነት አኳያ ሊያመጣ የሚችለውን ስጋት ከግምት ውስጥ ባስገባ አግባብ ከፌደራል እና ከክልል መንግስታት ጋር በመናበብ እየተሰራ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ለስደተኞች ከለላ መስጠት ብቻ ሳይሆን ተራማጅ የሆነ ሕግ በማውጣት ስደተኞችና ተቀባይ ማህበረሰቡን ያማከለ የዘላቂ ህይወት ማሻሻያ ፕሮጀክቶችን እየተገበረች መሆኑን ጠቅሰዋል። ለአብነትም ከአጋር አካላት ጋር በመቀናጀት በሶማሌ ክልል ዶሎ አዶ የሚገኙ ስደተኞችን ዘላቂ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የተከናወኑ የመስኖ ልማት ስራዎችን በስኬታማነት አንስተዋል። ስደተኞች በአካባቢና በተቀባዩ ማህበረሰብ ላይ የሚያደርሱትን ጫና ለመቀነስ የሚያስችሉ መሰል ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
በሕገ-ወጥ መንገድ የገቡ ከ148 ሚሊዮን ብር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸው የኮንትሮባድ እቃዎች ተያዙ
Jun 2, 2023 44
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ):- በሕገ ወጥ መንገድ የገቡ 148 ነጥብ 1 ሚሊዮን ብር ግምታዊ ዋጋ ያላቸው የኮንትሮባንድ እቃዎች መያዛቸውን የጉምሩክ ኮሚሽን አስታወቀ። ኮንትሮባንድ ዕቃዎቹ የተያዙት በድሬዳዋ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሲሆን የገቡትም በህገ ወጥ መልኩ ከጎረቤት አገር ሶማሊያ መሆኑ ተገልጿል። ከተያዙት የኮንትሮባንድ እቃዎች መካከል አልባሳት፣ ኤሌክትሮኒክስ፣ የመኪና መለዋወጫ፣ የመዋቢያ እቃዎች፣ መድኃኒቶች፣ የምግብ ነክ እቃዎች እና የቤት ውስጥ መገልገያ እቃዎች እንደሚገኙበት ገልጿል። እቃዎቹ የተያዙት ከሕብረተሰቡ በደረሰ ጥቆማ መሰረት የአገር መከላከያ ሰራዊት ፣የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ እና የጉምሩክ ኮሚሽን ሰራኞች በጋራ ባደረጉት ክትትል መሆኑን አመልክቷል። የኮንትሮባንድ አዘዋዋሪዎቹ በፀረ-ኮንትሮባንድ ግብረ ኃይሉ ክትትል እየተደረገባቸው መሆኑን ሲያውቁ ተሽከርካሪዎቹን ወደ ጫካ በማስገባት ለመሰወር ቢሞክሩም የተሰማራው ግብረ ኃይል ባደረገው የክትትል ስራ በቁጥጥር ስር ማዋል መቻሉ ተጠቁሟል። ኮሚሽኑ በዚህ የሕግ ማስከበር ዘመቻ ለተሳተፉ የድሬዳዋ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሰራተኞች እና አመራሮች፣ለአገር መከላከያ ሰራዊት፣ለኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ እና ለአካባቢው ሕብረተሰብ ምስጋና አቅርቧል። የኮንትሮባንድ እና ሕገወጥ ንግድ ስልቱ ተለዋዋጭ በመሆኑ ድርጊቱን ለመግታትና በአገር ኢኮኖሚ የሚያሳድረውን ተጽእኖ ለመከላከል ሁሉም ባለድርሻ አካላትና ሕብረተሰቡ የበኩሉን እንዲወጣም ጥሪ አቅርቧል።
በመጨረሻው ሩብ ዓመት የሚፈጸሙ ግዥዎችን ለማስቀረት የሚረዳ አሰራር ከቀጣዩ ዓመት ጀምሮ ተግባራዊ ይደረጋል
Jun 2, 2023 72
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ)፡- በመንግሥት ተቋማት በመጨረሻው ሩብ ዓመት የሚፈጸሙ ግዥዎችን ለማስቀረት የሚረዳ አሰራር ከቀጣዩ ዓመት ጀምሮ ሙሉ በመሉ ተግባራዊ እንደሚሆን የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን አስታወቀ። የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀጂ ኢብሳ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንዳሉት፤ ተቋማት የሚፈጽሙት ግዥ ባመዛኙ ያልታቀደና በአራተኛው ሩብ ዓመት ላይ ያተኮረ ነው። አራተኛ ሩብ ዓመት ላይ የሚፈጸሙ ግዥዎች ለመልካም አስተዳደር ችግሮች የመጋለጥ ዕድላቸው ሰፊ እንደሆነና "90 በመቶ የሚሆነው የኦዲተሮች ግኝት ተቋማት በመጨረሻው ሩብ ዓመት ከሚፈጸሙት ግዥ ጋር የተያያዘ ነው" ነው ያሉት። እንደ አቶ ሀጂ ገለጻ ተቋማት ምን መግዛት አለባቸው፣ መቼ ነው የሚገዛው፣ ከየት ነው የሚገዛው ፣ የጨረታ ሂደቱ እንዴት ይሆናል ፣ በሚለው ዙሪያ አቅዶ በመስራት በኩል ሰፊ ክፍተት እንደሚስተዋል ነው ያስረዱት። ከስልጠናዎች ጋር በተያያዘም ተቋማት የስልጠና መርሃ ግብሮችን በበጀት ዓመቱ መጀመሪያ ወይም በሐምሌ ፣ ነሃሴና መስከረም የዝግጅት ምዕራፍ ማካሄድ ያለባቸው ቢሆንም ይሄ እየተተገበረ አይደለም ሲሉ ነው የገለጹት። 65 በመቶ የሚሆነው የአገሪቷ በጀት የሚውለው ግዥ ላይ መሆኑን ጠቁመው በጀቱ በዕቅድ ላይ ተመስርቶ በአግባቡ ጥቅም ላይ ካልዋለ በአገርና ሕዝብ ላይ የሚያደርሰው ጉዳት ከፍተኛ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። በመጨረሻው ሩብ ዓመት ተቋማት የሚገዙበት ሥርዓት ከቀጣዩ ዓመት ጀምሮ እንደማይኖር የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ ያልታቀዱ ግዥዎችን ለማስቀረት የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ወሳኝ በመሆኑ በ2016 ዓ.ም በሁሉም የፌደራል ተቋማት ይተገበራል ብለዋል። እስካሁን 74 ተቋማት በኤሌክትሮኒክስ ግዥ ሥርዓት የታቀፉ ሲሆን ቀሪ 95 ተቋማት የግዥ ሥርዓቱን እንዲቀላቀሉ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። ለዚህም ይረዳ ዘንድ የመንግሥት ኤሌክትሮኒክስ ግዥ ሥርዓት እንዴት ነው የሚሰራው፣ምን ያስፈልጋል፣ በሚለው ላይ ለተቋማት ባለሙያዎችና አመራሮች ስልጠና እንደሚሰጥም አክለዋል። የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ሥርዓት ተግባራዊ ሲሆን ጥቃቅን እና አስገዳጅ ግዥዎችን ብቻ በአራተኛው ሩብ ዓመት ተቋማት እንዲገዙ ይፈቀዳል ብለዋል። በኤሌክትሪኒክስ ግዥ ሥርዓት በአሁኑ ወቅት 15 ሺህ አቅራቢዎች መኖራቸውን የገለጹት አቶ ሀጂ ስርዓቱ በቀጣዩ ዓመት ሁሉም የፌደራል ተቋማት በሂደቱ ስለሚካተቱም አቅርቦቱን የሚመጥን ስራ እየተሰራ ነው። ለዚህም ይረዳ ዘንድ በ2016 ዓ ም የአቅራቢዎችን ቁጥር ወደ 32 ሺህ ከፍ ለማድረግ በምዝገባና ስልጠና በመስጠት ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም አብራርተዋል።                                
የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ልዑክ በቻይና ይፋዊ የስራ ጉብኝት እያደረገ ነው
Jun 2, 2023 91
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ)፦የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የልዑካን ቡድን በቻይና ይፋዊ የስራ ጉብኝት በማድረግ ላይ ይገኛል። ጉብኝቱን እያደረጉ የሚገኙት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የማርኬቲንግ እና ኮሚዩኒኬሽን መምሪያ ከሌሎች የኮርፖሬሽኑ የስራ ኃላፊዎች ጋር ነው። በጉብኝቱ ቻይናውያን ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ይበልጥ መዋዕለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ ለማስቻል፣ አጠቃላይ የመንግስት የኢኮኖሚ ማሻሻያ ስራዎች ላይና ያሉ ምቹ የኢንቨስትመንት ሁኔታዎችን አስመልክቶ ከባለሀብቶች ጋር ውይይት እየተደረገ መሆኑ ተገልጿል። የኮርፖሬሽኑ ልዑክ በቻይና የኢትዮጵያ ኤምባሲ ጉብኝት ያካሄደ ሲሆን በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር ተፈራ ደርበው ጋር ስለ ኢንቨስትመንት ምልመላ ስራዎች እና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ውይይት አካሄዷል።   የተቋሙ የማርኬቲንግና ኮሚዩኒኬሽን መምሪያ ኃላፊው አቶ ዘመን ጁነዲን እና የልዑካን ቡድኑ ስለ ኮርፖሬሽኑ አጠቃላይ የሪፎርም ተግባራትና የስራ እንቅስቃሴ እንዲሁም የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ በ2015 ዓ.ም በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት የተደረጉ ቅድመ ዝግጅቶችንና ለኢንቨስተሮች የተዘጋጁ ምቹ ሁኔታዎችን አስመልክተው ማብራሪያ ሰጥተዋል። ልዑኩ በቻይና ቆይታው የተለያዩ ኢንዱስትሪ ፓርኮችን፣ ነጻ የንግድ ቀጣናዎችንና የኢንቨስትመንት ቦታዎችን እንደሚጎበኝ ከኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም