ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በሀረሪ ክልል ለቱሪዝም ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አበረታች ውጤት የታየበት ነው
May 4, 2026 37
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ በሀረሪ ክልል ለቱሪዝም ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አበረታች ውጤት የተመዘገበበት ነው ሲሉ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ገለጹ። በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር የተመራው የአስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች የልዑካን ቡድን በሀረር ኢኮ ፓርክ የጅብ ትርኢትን ተመልክተዋል።   ከንቲባው በጉብኝታቸው ላይ እንደተናገሩት በክልሉ መሰል የቱሪዝም መስህቦችን ለማስፋፋት የተደረገው ጥረት አበረታች ውጤት የታየበት ነው። በክልሉ የተገነባው የጅብ ትርዒት ማሳያ ፓርክም ለቱሪስቶች ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ያሉት ከንቲባው ይህም የቱሪዝም ዘርፉን በማጎልበት ከተማዋን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ የሚያደርግ መሆኑን ገልፀዋል።   የሀረር ከተማን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎችም ውጤታማና አበረታች መሆናቸውን እንደተመለከቱ ገልጸዋል። በጉብኝቱ ላይ የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪን ጨምሮ የሀረሪ ክልል እና የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ውጤቶችን በማስፋት የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት ማፋጠን ያስፈልጋል
May 4, 2026 59
አዲስ አበባ፣ሚያዚያ 26/2018 (ኢዜአ)፦በሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የተገኙ ውጤቶችን በማስፋት የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት ማፋጠን እንደሚያስፈልግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የገንዘብ ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማትን የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርት ገምግሟል።   የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በሪፖርታቸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በዘንድሮው በጀት ዓመት 10 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት ማስመዝገብ የሚያስችል ስኬት እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር በተሰራው ሥራም በታኅሳስ 2018 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ የዋጋ ግሽበቱን ዘጠኝ ነጥብ ሰባት በመቶ በማድረስ ወደ አንድ አሃዝ ማውረድ መቻሉን አመልክተው፤ የመጋቢት ወርም ወደ ዘጠኝ ነጥብ አራት በመቶ መውረዱን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት መንግስት ከብሔራዊ ባንክ ምንም ዓይነት ብድር አልወሰደም ያሉት ሚኒስትሩ፤ ከብሔራዊ ባንክ ቀጥታ የሚወሰደው ብድር እንዲቆም መደረጉም የዋጋ ንረትን እንዲቀንስ አድርጓል ብለዋል። በቡድን 20 የጋራ ማዕቀፍ አማካኝነት ኢትዮጵያ የዕዳ ሽግሽግ እፎይታ እንድታገኝ ስኬታማ የሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ ድርድር መደረጉን ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብሩ በጥብቅ የፊስካል ፖሊሲ ቁጥጥርና የቁጠባ ዲሲፕሊን በመመራቱ ኢትዮጵያን ከአፍሪካ ቀዳሚ ዕድገት የምታስመዘግብ ሀገር እያደረጋት መሆኑን አንስተዋል። የምክር ቤቱ አባላትም፤ የሚኒስቴሩን የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርት መነሻ በማድረግ በዋጋ ግሽበት፣ የዕዳ ሽግሽግና ተያያዥ የኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ ጥያቄና አስተያየት አቅርበዋል። የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በምላሻቸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የሚያስከትለውን ጫና ለመቀነስ በደመወዝ ጭማሪ፣ ማዳበሪያ፣ ነዳጅ፣ የምግብ ዘይትና መሰረታዊ ሸቀጦች ላይ መንግስት ድጎማ እያደረገ ነው ብለዋል። በሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ በተደረጉ ስኬታማ ድርድሮችም ኢትዮጵያ ከጣሊያንና ፈረንሳይ ጋር የዕዳ ሽግሽግ ስምምነት መፈረሟን አስረድተዋል። ከቻይና ጋርም የዕዳ ሽግሽግ ስምምነት መፈረም የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው ያሉት የገንዘብ ሚኒስትሩ፤ ከዩሮ ቦንድ አበዳሪዎች ኮሚቴ ጋር ያለው ድርድር መቀጠሉን ገልጸዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ደሳለኝ ወዳጄ፤ ሪፖርቱ ቀጣይነት ያለው ዕድገት መኖሩን የሚያሳይ ነው ብለዋል። በቀጣይም በዋጋ ንረትን፣ ዕዳ ሽግሽግ፣ በወጪና ገቢ ንግድ አፈፃጸም የተገኙ ውጤቶችን በማጠናከር የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙን ውጤቶችን በማስፋት ዕድገትን ማስቀጠል እንደሚገባ አሳስበዋል።
ኮርፖሬሽኑ በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ወደ ተግባር ምዕራፍ ተሸጋግሯል 
May 4, 2026 94
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ ኮርፖሬሽኑ ባስቀመጠው ራዕይ መሠረት በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ከፍተኛ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቶ አሁን ላይ ወደ ተግባር ምዕራፍ መሸጋገሩን የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ረሻድ ከማል ገለጹ። የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን ጁባ ከተማ በቤት ግንባታ ዘርፍ መሰማራት የሚያስችለውን ታሪካዊ ስምምነት ተፈራርሟል። በሁለቱ ሀገራት መካከል በመሪዎች ደረጃ የጋራ የልማት ትብብር በሚፈልጉ ጉዳዮች ላይ አብሮ ለመስራት ስምምነት መደረሱን ተከትሎ በኮርፖሬሽኑ እና በደቡብ ሱዳን ማዕከላዊ ኢኳቶሪያል ግዛት መካከከል በቤት ልማት ላይ በጋራ መስራት የሚያስችል ስምምነት ተፈጽሟል፡፡   በኢትዮጵያ ፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን እና በደቡብ ሱዳን የማዕከላዊ ኢኳቶሪያል ግዛት መንግሥት መካከል የተደረገው ይህ የመግባቢያ ሰነድ፣ በጁባ ከተማ በቤቶች ልማትና አስተዳደር ዘርፎች በጋራ መሥራት የሚያስችል መሠረት ጥሏል ነው ያለው ኮርፖሬሽኑ። ስምምነቱን የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) እና የማዕከላዊ ኢኳቶሪያ ግዛት መንግሥት አስተዳዳሪ ኢማኑኤል አዲል በይፋ መፈረማቸውን ኢዜአ ከኮርፖሬሽኑ ያገኘው መረጃ ያመላክታል። ይህ ውል ኮርፖሬሽኑ ያለውን የረጅም ጊዜ ልምድና የቴክኒክ አቅም በመጠቀም በጁባ ከተማ ዘመናዊ የመኖሪያ ቤቶች፣ የንግድ ሕንፃዎችና የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ግንባታ እንዲያከናውን ሰፊ መንገድ እንደሚከፍትም ተመላክቷል። ዋና ሥራ አስፈጻሚው በሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደተናገሩት፣ ኮርፖሬሽኑ ባስቀመጠው ራዕይ መሠረት በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ከፍተኛ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቶ አሁን ላይ ወደ ተግባር ምዕራፍ ተሸጋግሯል።   ኮርፖሬሽኑ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ያላቸውና አዋጭ በሆኑ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል። በደቡብ ሱዳን የማዕከላዊ ኢኳቶሪያ ግዛት መንግሥት አስተዳዳሪ ኢማኑኤል አዲል በበኩላቸው፣ በኢትዮጵያ እየተመዘገበ ያለው ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና ፈጣን የከተሞች ለውጥ ለመላው አፍሪካውያን ተምሳሌት መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታም በርካታ የልማት ሥራዎችን ተዘዋውረው መመልከታቸውን ተናግረዋል። በተለይም በቤት ልማት ዘርፍ በኢትዮጵያ ያለውን ተሞክሮ ከኮርፖሬሽኑ ጋር በመሆን በጁባ ከተማና በግዛቱ ተግባራዊ ለማድረግ እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል።   ስምምነቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ትስስር ከማጠናከር ባሻገር፣ ኮርፖሬሽኑ በቤት አስተዳደርና ልማት ያለውን ውጤታማ ተሞክሮ ለግዛቱ ባለሙያዎች የሚያጋራበትንና የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን የሚሰጥበትን ዕድል ያመቻቻል ብለዋል። የስምምነቱን አፈጻጸም በቅርበት የሚከታተል፣ ዝርዝር የፕሮጀክት ሰነዶችን የሚያዘጋጅና አጋዥ የመፍትሔ ሐሳቦችን የሚያመነጭ የጋራ ቴክኒክ ኮሚቴ እንዲቋቋም መወሰኑም ተመላክቷል። ይህ ስምምነት የሁለቱ ሀገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ከማሸጋገሩ በላይ፣ የኢትዮጵያን የቤቶች ልማት ተሞክሮ ወደ ጎረቤት ሀገራት ለማስፋፋት ትልቅ መነቃቃትን እንደሚፈጥርም ተገልጿል።
ኢትዮጵያ የቱሪዝም ጸጋዎቿን እንድትጠቀም የግል ዘርፉ የሆቴልና የመዳረሻ ልማት ወሳኝ ነው
May 4, 2026 68
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የቱሪዝም ጸጋዎች በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል የግል ዘርፉ በሆቴልና በመዳረሻ ልማት ላይ የሚኖረው ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባሕር ዳር ታሪኳን ሳትለቅ ዘመኑን እየዋጀች መሆኑን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል። ቀደም ሲል የከተማዋ ትዝታ በነበረው በታሪካዊው ጣና ሆቴል ሥፍራ ዓለም አቀፍ ደረጃን ያሟላ የፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን (Four Points by Sheraton) ሆቴል የግንባታ ፕሮጀክት በይፋ መጀመሩን አመልክተዋል።   በሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ የሚገነባው ይህ የሆቴል ፕሮጀክት ከተማዋን የቱሪዝም ሠገነት እንደሚያደርጋት ተናግረዋል። በርካታ አገልግሎቶችን አሟልቶ በአሥራ ስምንት ወራት ግንባታው የሚጠናቀቀው ይህ ሆቴል፣ የግል ባለ ሀብቱ በሀገሪቱ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ውስጥ ያለውን ሚና በተግባር የሚያሳይ ነው ብለዋል።   ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በተለያዩ ዘርፎች እያመጣ ያለው ለውጥ የሚደነቅ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፣ ይህ የሆቴል ግንባታም ለባሕር ዳር በጸጋ ላይ ጸጋ የሚጨምር መሆኑንም ነው የተናገሩት። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ፕሮጀክቱን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት ለከተማዋና ለሀገሪቱ ሕዝብ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
በዞኑ ሰላምን በማጽናት የማህበረሰቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ
May 4, 2026 69
ደብረ ማርቆስ፣ሚያዚያ 26/2018 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ጎጃም ዞን ሰላምን በማጽናት የማህበረሰቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገለጸ።‎ በዞኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተከናወኑ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ላይ የሚመክር መድረክ በደብረ ማርቆስ ከተማ ተካሄዷል። ‌‎በመድረኩም የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኑርልኝ ብርሃኑ እንዳሉት፤ በበጀት ዓመቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ሰላምን በማስፈን ለልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ረገድ አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል። በቀሪ ወራትም ተጨማሪ ስራዎችን በማከናወን የበለጠ ስኬት ለማስመዝገብ ርብርብ እንደሚደረግ ጠቅሰው፤ ‎መድረኩም በስራ አፈፃፀም የታዩ ጥንካሬዎችን በማስቀጠል ድክመቶችን ለማረም ታሳቢ ያደረገ ነው ብለዋል። የዞኑ ሰላምና ጸጥታ መምሪያ ሃላፊ አቶ ደምስ አለኸኝ በበኩላቸው፤ በዞኑ የሰፈነው ሰላም የተለያዩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን ለማከናወን ማስቻሉን ጠቁመዋል። በዞኑ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን የማፋጠን ተግባር ህብረተሰቡን ባሳተፈ አግባብ እየተከናወነ ሲሆን ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉም አረጋግጠዋል። በዞኑ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ለተሻሻሉ አሰራሮችና ቴክኖሎጂዎች ትኩረት መሰጠቱን ያነሱት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ ጥላሁን ንጋቱ ናቸው። በዚህም በ2017/18 የምርት ዘመን የሰብል ምርታማነትን በሄክታር ከ35 ወደ 38 ኩንታል ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል። በመኸር ወቅቱ ከለማው ከ640 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ከ23 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን ጠቅሰው፤ በመስኖ ልማቱም እስካሁን ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተገኝቷል ብለዋል። የአማራ ክልል ምክር ቤት የግብርና፣ የአካባቢ ጥበቃ እና ውሃ ስራዎች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ከፍያለው ሙላቴ፤ በልማትና መልካም አስተዳደር ስራዎች የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት እንዲጠናከሩ አሳስበዋል።
በባህርዳር ከተማ ጸጋን ወደ በረከት የሚቀይሩ ግዙፍ የቱሪዝም ልማት ፕሮጀክቶች እየተገነቡ ነው 
May 4, 2026 90
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ በባህርዳር ከተማ የቱሪዝም ጸጋዎችን ወደ በረከት የሚቀይሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች እየተገነቡ እንደሚገኙ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በባህርዳር ከተማ በ3 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር የሚገነባውን ፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና የሆቴል ፕሮጀክት ግንባታን አስጀምረዋል።   በታሪካዊው ጣና ሆቴል ባለበት ሥፍራ ላይ በሚድሮክ ኢንቨስትመንት የሚገነባው ይህ ዓለም አቀፍ ሆቴል በ18 ወራት ውስጥ ተገንብቶ እንደሚጠናቀቅ ተገልጿል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ​ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት ለባህርዳር ከተማና ለሀገራችን የቱሪዝም መዳረሻነት ከፍታና ለኢኮኖሚ መነቃቃት ትልቅ ብስራት ነው ብለዋል። የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በእርሻ፣ በማዕድንና በሌሎች ዘርፎች የሚያስመዘግበው አስደናቂ ስኬት የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚ ዕድገት የሚያበረክተውን ከፍተኛ ሚና በተግባር የሚያረጋግጥ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የኢንቨስትመንት ግሩፑ በፈታኝ ወቅት ቀድሞ በመገኘትና ክፍተቶችን በመሙላት በኩል የላቀ ተምሳሌትነት መገለጫ እንደሆነም ተናግረዋል። በባህርዳር ግንባታው የተጀመረው ሆቴል ሲጠናቀቅም ጸጋን ወደበረከት በመቀየር ኢትዮጵያ ዘመኑን የዋጀና ዘላቂ ኢኮኖሚ ለመገንባት በጀመረችው ጉዞ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን አንስተዋል።   በተለይም በአካባቢው ካሉ የተፈጥሮና ሠው ሠራሽ የቱሪዝም ፀጋዎች ጋር ተዳምሮ ለባህርዳርና ለአካባቢው ዕድገት ትልቅ ዕድል ይዞ እንደሚመጣም አስረድተዋል። መንግሥት የኢትዮጵያና ከተሞቿን የቱሪዝም መዳረሻነት ከፍ የሚያደርጉ ትውልድ ተሻጋሪ ፕሮጀክቶች እንዲሳኩ ለማድረግ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና ሆቴል ፕሮጀክት በፍጥነት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ለማብቃት መትጋት እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል። የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፥ ኩባንያው መንግሥት የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ለቱሪዝም ዘርፉ መነቃቃት የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ነው ብለዋል።   በባህርዳር የሚገነባውን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ሆቴል በ18 ወራት ውስጥ ለማጠናቀቅ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። ሚድሮክ በተለያዩ ከተሞች ለኢትዮጵያ ቱሪዝም ዕድገት ገንቢ ሚና የሚወጡ ዘመናዊ ሆቴሎችን እየገነባ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። በ3 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ወጪ የሚገነባው የፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና ሆቴል ​በ32 ሺህ 440 ካሬ ሜትር ላይ የሚያርፍ ሲሆን ​120 ዘመናዊ መኝታ ክፍሎችና አራት ዓለም አቀፍ ሬስቶራንቶች፣ ​ከ1 ሺህ በላይ ሰዎችን ማስተናገድ የሚችል ትልቅ አዳራሽና የመዋኛ ገንዳን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶችን አካቷል።​
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ቀጣናዊ ደኅንነትን ለማስጠበቅ እና ለጋራ ዕድገት ወሳኝ ነው
May 4, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ለምስራቅ አፍሪካ ቀጣናዊ ትስስር፣ ለጋራ ተጠቃሚነትና ለቀጣናው ደኅንነት መጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ምሁራን ገለጹ። ኢዜአ ያነጋገራቸው ምሁራን እንደገለጹት፤ የሀገሪቱ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የህልውና እና የቀጣናዊ እድገት ጉዳይ ነው። በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሀብት መምህርና ተመራማሪ ዱጋሳ ሙሉጌታ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገዶችን ተከትላ የባህር በር ለማግኘት የምታደርገው ጥረት የሚበረታታ ነው።   የባህር በር ማግኘት የህልውና ጉዳይ መሆኑን አስረድተው፤ ለወጪና ገቢ ንግድ እንቅስቃሴ እንዲሁም ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ፍትሐዊ፣ ሕጋዊ፣ ታሪካዊና መልክዓ-ምድራዊ እውነታን መሰረት ያደረገ መሆኑንም አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ቀጣናዊ ትስስርን በማጎልበት፣ በጋራ ተጠቃሚነት መርህ ላይ የተመሠረተ መሆኑንና ለቀጣናው ሀገራት ዘላቂ ሰላምና የጋራ ልማት የላቀ ጠቀሜታ እንዳለው አስረድተዋል። በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የውሃ ሀብት መምህርና ተመራማሪ ሲሳይ ደመቁ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የባህር በር ከሸቀጥ ዝውውር ባለፈ የሃሳብ፣ የቴክኖሎጂና የቱሪዝም ፍሰትን በማሳለጥ በኩል ያለውን ፋይዳ አብራርተዋል።   የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለምስራቅ አፍሪካ ቀጣናዊ ትስስር፣ ለጠንካራ ደህንነት፣ ለኢኮኖሚና ለቴክኖሎጂ ዕድገት ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑንም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት የሎጂስቲክስ ወጪን በመቀነስ የገቢና ወጪ ንግድ ተወዳዳሪነትን ከማሳደግ ጎን ለጎን፣ ለቀጣናው ደህንነት መጠበቅ ትልቅ ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል።
ለኢንቨስትመንት የሚውሉ ሀብቶችን ለማልማት በሚደረገው ጥረት ባለሀብቱ ሚናውን ሊያጠናክር ይገባል
May 4, 2026 66
ባሕር ዳር፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፡- በአ‎‎ማራ ክልል ለኢንቨስትመንት የሚውሉ ሀብቶችን ለይቶ በማልማት ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማጎልበት እየተደረገ ባለው ጥረት ባለሀብቱ ሚናውን ሊያጠናክር እንደሚገባ ርዕሠ መሥተዳደር አረጋ ከበደ አሳሰቡ።   በባሕር ዳር ከተማ መሬት ወስደው በኢንቨስትመንት ዘርፍ ከተሰማሩ ባለሃብቶች ጋር የውይይት መድረክ ተካሂዷል። ‎ ርዕሠ መሥተዳድሩ በዚሁ ወቅት፤ ‎ክልሉ በግብርና፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም እና በሌሎች ዘርፎች የዕምቅ ሃብቶች ባለቤት በመሆኑ ይህን ሀብት በማልማት ክልሉንና ሀገሪቱን የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ባለሃብቱ ሚናውን ሊያጠናክር እንደሚገባ ገልጸዋል። በተለይም በግብርና ዘርፍ ክልሉ ለኤክስፖርትና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ምርቶች በብዛትና በጥራት የሚመረትበት በመሆኑ ባለሃብቶች በዘርፉ ተሳትፏቸውን እንዲያጠናክሩም ጠይቀዋል ። ‎ በማዕድን ዘርፍም የኦፓል፣ የወርቅ፣ የብረት፣ የድንጋይ ከሰልና ለሌሎች አገልግሎት የሚውሉ ሃብቶች ባለቤት በመሆኑ፤ ሃብቱን አልምቶ ለመጠቀም ባለሃብቶች በዘርፉ የበለጠ ሊሳተፉ እንደሚገባም አመልክተዋል። ‎ የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው ወደምርት የተሸጋገሩና በግንባታ ላይ የሚገኙ ባለሃብቶች ሥራቸውን በማጠናከር የክልሉን ልማት እንዲያፋጥኑ አሳስበዋል። ‎ የክልሉ መንግሥት በዘርፉ የሚስተውሉ የብድር፣ የኤሌክትሪክ አግልግሎትና የመንገድ መሠረተ-ልማት አቅርቦት ክፍተቶችን ለመቅረፍ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ አረጋግጠዋል።   ‎የባሕር ዳር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በበኩላቸው፤ አሥተዳደሩ ከተማዋን የቱሪዝምና የኢኮኖሚ ማዕከል ለማድረግ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በከተማዋ አዲስ ለኢንዱስትሪ መንደር የሚሆን ተጨማሪ 300 ሔክታር መሬት በመለየት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ እስካሁን 122 ሔክታር መሬት ተሸንሽኖ ለባለሀብቶች ዝግጁ መደረጉን አስታውቀዋል። በከተማዋ የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው በተለያዩ ምክንያቶች ሥራ ያቆሙ ባለሃብቶች ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን ገልፀው፤ ዘንድሮ 23 ፋብሪካዎች ወደማምረት እንዲገቡ መደረጉን አንስተዋል።
የኮሪደር ልማቱ ለቱሪዝምና ኢንቨስትመንት መስፋፋት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
May 4, 2026 123
ባሕር ዳር፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ለቱሪዝምና ኢንቨስትመንት ዘርፉ መስፋፋት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የክልሉ ከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ገለፀ። የቢሮው ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኮሪደር ልማቱ የተጎሳቆሉ ከተሞችን በማልማት ውበታቸው እንዲወጣ አድርጓል። የከተሞችን የኮንስትራክሽን ዘርፍ ከማነቃቃት ባለፈ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴያቸው እንዲነቃቃ ማስቻሉንም ጠቁመዋል። ከተሞች ለነዋሪዎች የተመቹ እንዲሆኑ ማድረጉን ገልጸው፤ ለቱሪዝም ዘርፉ ማደግና የከተሞችን የኢንቨስትመንት ፍሰት በማሳለጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም አንስተዋል። በያዝነው ዓመት በ106 ሔክታር ላይ የኮሪደር ልማት ለመሥራት መታቀዱን እና እስካሁን በ80 ሔክታሩ ላይ መከናወኑን አረጋግጠዋል። በዚህ ሥራም የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገድን ጨምሮ 108 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ልማት መከናወኑን አስታውቀዋል። በተሠራው የኮሪደር ልማት 10 የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች፣ 168 ደረጃቸውን የጠበቁ ካፍቴሪያዎች፣ የሕጻናት መዝናኛዎች፣ የአረጋውያን ማረፊያዎችና ሌሎች ማኅበራዊ አገልግሎት ሰጪ ስፍራዎች መካተታቸውን አብራርተዋል። ለኮሪደር ልማቱ ከ6 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ መደረጉን ገልጸው፤ ከዚህ ውስጥ 3 ነጥብ 4 ቢሊዮኑ ሕብረተሰቡ በገንዘብ፣ በጉልበቱና ቁሳቁስ ተሳትፎ ያደረገበት መሆኑን አስገንዝበዋል። በኮሪደር ልማቱ ለ112 ሺህ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩንም አመላክተዋል። በቀጣይ ልማቱን ወደ ሌሎች ከተሞች የማስፋቱ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው ያመላከቱት።
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በአሲድ የተጠቃ መሬትን በኖራ በማከም የሰብል ምርታማነትን ለማሳድግ እየተሰራ ነው
May 4, 2026 65
ጎንደር፤ሚያዚያ 26/2018(ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በመጪው የመኸር ወቅት ከ12ሺህ ሄክታር በላይ በአሲድ የተጠቃ መሬትን በኖራ በማከም የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ የመምሪያው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ ለኢዜአ እንደገለጹት የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ ከተቀመጡ ስትራቴጂዎች አንዱ አሲዳማ የእርሻ መሬትን በኖራ ማከም ነው፡፡ በዚህም በመኸር ወቅት ሙሉ በሙሉ እና በከፊል በአሲድ ተጠቅተው ምርት መስጠት ያቆሙ የእርሻ መሬቶችን ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ በማከም የሰብል ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በእስካሁኑ ጥረት ከ7 ሺህ ኩንታል በላይ ኖራ በመርጨት 8 ሺህ ሄክታር መሬት ለማከም መቻሉን ገልጸው፣በቀሪ ወራትም ተጨማሪ የእርሻ መሬት ለማከም ሥራው ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል። አቶ ንጉሴ እንዳሉት፥ ካለፉት ዓመታት ተሞክሮ እንደታየው በኖራ ከታከመ መሬት በሄክታር እስከ 15 ኩንታል የምርት ጭማሪ ለማግኘት ተችሏል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ2026 የAPEX መንገደኞች ምርጫ 'በአፍሪካ ምርጡ አየር መንገድ' ሽልማትን አሸንፏል
May 4, 2026 123
አዲስ አበባ፣ሚያዚያ 26/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ2026 የAPEX መንገደኞች ምርጫ 'በአፍሪካ ምርጡ አየር መንገድ' ሽልማትን አሸንፏል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ2026 የAPEX መንገደኞች ምርጫ 'በአፍሪካ ምርጡ አየር መንገድ' (Best Airline in Africa) ሽልማትን በማሸነፍ የአቪዬሽን መሪነቱን አረጋገጠ። ይህ እውቅና አየር መንገዱ በመላው ዓለም በሚያደርጋቸው በረራዎች ቀልጣፋ፣ ምቹ እና አስተማማኝ አገልግሎት ለመስጠት ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ሲሆን፤ ሽልማቱም ሙሉ በሙሉ በመንገደኞች እውነተኛ የጉዞ ተሞክሮ በተሰጠ ድምፅ አማካኝነት ነው። አየር መንገዱ 'ራዕይ 2040' በተሰኘው ስትራቴጂካዊ ዕቅዱ በዓለም ካሉ 20 ቀዳሚ የአቪዬሽን ግሩፖች አንዱ ለመሆን እየሠራ ሲሆን፣ በቶጎ፣ ማላዊ፣ ዛምቢያ እና ኮንጎ ከሚገኙ አየር መንገዶች ጋር በመተባበር የበርካታ ማዕከላት (multi-hub) ስትራቴጂን በመተግበር ላይ እንደሚገኝም ታውቋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ለሀገር ግንባታ የሚፈጥሩ አዕምሮዎችና የሚሠሩ እጆች ዋነኛ ምሰሶዎች ናቸው-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 4, 2026 120
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ለሀገር ግንባታ የሚፈጥሩ አዕምሮዎችና የሚሠሩ እጆች ዋነኛ ምሰሶዎች ናቸው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ የሥራና ክህሎት ቢሮ ያዘጋጀው 16ኛው ከተማ አቀፍ የቴክኒክና ሙያ ሳምንት "የቴክኖሎጂ ልህቀት ለሀገር ብልፅግና" በሚል መሪ ሐሳብ በአራዳ ፓርክ ተከፍቷል።   የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች በዚሁ ወቅት፤ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ኢትዮጵያ በዘርፉ እያሳየች ያለችውን ትልቅ እመርታ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። ሀገር በሚፈጥሩ አዕምሮዎችና በሚሠሩ እጆች ይገነባል ያሉት ከንቲባዋ፤ለዚህም የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች እያከናወኑ ላለው ተግባር ዕውቅና መስጠት እንደሚገባ ተናግረዋል። ሀገር በልጆቿ ጥረት እንደምትገነባ ገልጸው፤በተለይም በቴክኖሎጂ ዘርፍ እየታየ ያለው ለውጥ ተስፋ ሰጪ መሆኑን ጠቁመዋል። የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ለሀገር የኢኮኖሚ ዕድገትና ለኢንዱስትሪ ሽግግር መሠረት የሚጣልበት መሆኑንም ገልጸዋል።   ቀደም ሲል ከውጭ ሀገር በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ሲገቡ የቆዩ ምርቶች አሁን ላይ በሀገር ውስጥ በቴክኒክና ሙያ ተቋማት መመረት መጀመራቸውን ጠቅሰዋል። በተለይም በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ ግዙፍ የመሠረተ ልማት ሥራዎች የዘርፉ ባለሙያዎች ዕውቀታቸውና ጥበባቸው በተግባር እየታየ መሆኑን ገልጸዋል። ምርቶቹን በሀገር ውስጥ ከመተካት ባለፈ ዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ተወዳዳሪ በማድረግ ወደ ውጭ መላክ ላይ ትኩረት ሊደረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። ይህ ሂደት ሀገራችን በራሷ አቅም እንድትቆም ትልቅ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፤ የከተማ አስተዳደሩ እነዚህን የፈጠራ ሥራዎች ለማስፋፋት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።   በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ይታወቃል። ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራርና ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ የሰው ሠራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ላለው የላቀ ሚና የተሰጠ ዕውቅና መሆኑ በወቅቱ ተገልጿል። ሹመቱ ኢትዮጵያ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን ሥነ ምግባራዊ መርሆች በተከተለ መልኩ በማልማት፣በመመራመር እንዲሁም ተግባራዊ በማድረግ በኩል ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር እንድትሆን ለተሰሩ ሥራዎች ዕውቅና የሰጠ ነው በሚል መገለጹ ይታወሳል።
የግብርና ኢንሼቲቮችን በማስፋት ተረጂነትን ለመቅረፍ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
May 4, 2026 72
ሐረር፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በግብርናው ዘርፍ የተጀመሩ ኢንሼቲቮችን በማስፋትና ምርታማነትን በማሳደግ ሕዝቡን ከተረጂነት የማላቀቅ ሥራ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሠ መሥተዳድር ሮዛ ኡመር ገለጹ።   ለእርሻ የሚውል ሁሉንም መሬት በማረስ ምርትና ምርታማነትን የማጎልበት ሥራ ተግባራዊ መደረጉን የገለጹት ወ/ሮ ሮዛ፤ የሚከናወኑ የግብርና ሥራዎችን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ የመስኖ ግድቦች ግንባታ እየተከናወነ ነው ብለዋል። በዚህም መሠረት አርሶ አደሩ የከርሰ ምድር ውኃን የፀሐይ ኃይል በመጠቀም አትክልትና ፍራፍሬ እንዲያለማ መደረጉን ለኢዜአ ተናግረዋል። በሌማት ትሩፋት ዘርፍ የሚገኘውን ምርታማነት ከማሳደግ አኳያም በወረዳዎች ሼዶችን በመገንባት ለወጣቶች እንዲተላለፍ መደረጉን እና ምርጥ ዝርያ ያላቸው የዶሮ ጫጩቶች ለአርሶ አደሩ መሠራጨታቸውን ገልጸዋል። በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ረገድም ሥራዎች በየዓመቱ እያደጉ መምጣታቸውን ጠቅሰው፤ በዘንድሮው በጋ በክልሉ አመርቂ የተፋሰስ ልማት ሥራ መከናወኑን አስታውቀዋል። በዚህም ተረጂ የነበሩ አርሶ አደሮች ምርታማነትን በማጎልበት ከራሳቸው አልፈው ምርታቸውን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
የጣና ሐይቅ ተቀድቶ የማያልቅ የልማት ምንጭ፤ የማይደበዝዝ የውበት ጮራ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 3, 2026 182
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018(ኢዜአ)፦ የጣና ሐይቅ ተቀድቶ የማያልቅ የልማት ምንጭ፤ የማይደበዝዝ የውበት ጮራ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው እንዳስታወቁት ለባሕር ዳርና ለአካባቢው ዘርፈ ብዙ ትሩፋት ይዞ የመጣውን ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ዛሬ መርቀን ለአገልግሎት ከፍተናል። ዳርቻ የለሽ የተፈጥሮ ውበት ከሰው ልጆች ትጋት ጋር ሲደመር ምን ውጤት እንደሚገኝ ባሕር ዳር ማሳያ ናት ሲሉም ተናግረዋል።   ባሕር ዳር በኢትዮጵያ ትልቁ ሐይቅ እና በዓለም ትልቁ ወንዝ የሚገናኙባት ከተማ ናት ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዙሪያዋ ፈጣሪ የሰውን መንፈስ በነፍስም በሥጋም ለማደስ የፈጠረው አካባቢ ነው በወዲያ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት አለ ብለዋል በመልዕክታቸው። ተሻግሮ የጎንደር ፋሲለደስ ደረቱን ነፍቶ ይታያል መነሻ በወዲህ በገበታ ለሀገር ኢኒሼቲቭ ተጠንስሶ በአቶ ካሣሁን(ቢአይካ) የተገነባው የፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ይገኛል፤ በመሐል ዓባይና ጣና ናቸው ሲሉም ገልጸዋል። ዛሬ የመረቅነው የፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ለከተማዋና ለሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ተጨማሪ የውበት እና የልማት ከፍታ ነው ብለዋል። መንግሥት ለቱሪዝም መዳረሻዎች የሰጠው ትኩረት ምን ውጤት እንዳመጣ በገሐድ የሚነበብበት ፕሮጀክት ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአካባቢውን የቱሪዝም መሥመርና ሠንሠለት የሚያጠናክር ማረፊያና መዳረሻም ነው።   ሪዞርቱ ዘመናዊ እና ቅንጡ የእንግዳ ማረፊያዎች፣ የመዝናኛ ሥፍራዎች፣ ሱቆች ፣ አምፊ ቴአትር እና መሰል መሠረተ ልማቶችን አሟልቶ፣ ጣናን ተንተርሶ የተሠራ ሪዞርት ነውም ብለዋለ። በባሕር ዳር ኢንቨስት ለማድረግ ሥራ የጀመሩና መሬት የተረከቡ ኢንቨስተሮች እንደ ፈለገ ግዮን ሥራዎቻቸውን በፍጥነት እንዲፈጽሙ አደራ እንላለን ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።
በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ተመርቆ የተከፈተው ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት…
May 3, 2026 173
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትን መነሻ በማድረግ በገበታ ለሀገር ፕሮጀክት አካል ሆኖ በግል ኢንቨስትመንት በባህር ዳር ከተማ የተገነባውን የፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት በዛሬው ዕለት መርቀው ከፍተዋል፡፡   ስለፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት በጥቂቱ፦ ✅በባህር ዳር ከተማ በጣና ሐይቅ ደቡባዊ ዳርቻ ላይ ተገንብቷል፤ ✅በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "ገበታ ለሀገር" እቅድ መሰረት በሐይቁ ሌላኛው አቅጣጫ ከሚገኘው የጎርጎራ ብርሃን (ጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት) ጋር በመቀናጀት የጣናን የቱሪዝም ቀጣና ለማነቃቃት የታለመ ነው፤ ✅ 4 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር ወጪ ተደርጎበታል፤ ✅ በሁለት ዓመት ከስድስት ወር (30 ወራት) ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ለምረቃ በቅቷል፤ ✅በሀገር በቀሉ ባለሀብት በአቶ ካሳሁን ምስጋናው (የቤአኢካ ንግድና ኢንቨስትመንት መሥራች) አማካኝነት በግል ኢንቨስትመንት የተገነባ ነው፤ ✅ሪዞርቱ አዲስ በተቋቋመው ሮዳ ሆስፒታሊቲ ግሩፕ ስር ይተዳደራል፤ ✅ሮዳ ሆስፒታሊቲ ግሩፕ ይህንን አዲስ ሪዞርት እና የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትን በአንድ ላይ በማስተዳደር የቀጣናውን የሆስፒታሊቲ አገልግሎት ይመራል፤ ✅ኢኮ-ሪዞርቱ፦ የተፈጥሮ አካባቢን በጠበቀ መልኩ የተገነባ የቱሪስት መዳረሻ ነው፤ ✅በግል ኢንቨስትመንት ቢገነባም፣ በመንግሥት የገበታ ለሀገር ማዕቀፍ ኢኒሼቲቮች ውስጥ ተካትቶ የተመራና ትኩረት የተሰጠው ፕሮጀክት ነው፤ ✅ሪዞርቱ ለአማራ ክልልም ሆነ ለሀገሪቱ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ አዲስ የገቢና የሥራ ዕድል ምንጭ እንደሚሆንም ይጠበቃል።
በአማራ ክልል ተፈጥሯዊና ታሪካዊ ጸጋዎችን ለዓለም የሚያስተዋውቁ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎች እውን እየሆኑ ነው - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
May 3, 2026 151
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018(ኢዜአ)፦ መንግሥት ለቱሪዝም ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረት የአማራ ክልልን ተፈጥሯዊና ታሪካዊ ጸጋዎች ለዓለም የሚያስተዋውቁ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎች ግንባታ እውን እየሆነ ነው ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩመህ​ በገበታ ለሀገር ኢኒሼቲቭ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትን መነሻ በማድረግ በባህር ዳር ከተማ ጣና ዳርቻ በባለሀብቱ ካሳሁን ምስጋናው የተገነባውን ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ዛሬ መርቀው ከፍተዋል።   በመርኃ ግብሩ የአማራ ክልል እና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ አባ ገዳዎች፣ ባለሀብቶችና የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች ተገኝተዋል። በባህር ዳር ከተማ በጣና ሐይቅ ደቡባዊ ዳርቻ ላይ የተገነባው ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "ገበታ ለሀገር" እቅድ መሰረት በሐይቁ ሌላኛው አቅጣጫ ከሚገኘው የጎርጎራ ብርሃን (ጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት) ጋር በመቀናጀት የጣናን የቱሪዝም ቀጣና ለማነቃቃት የታለመ ነው። ይሄው በአራት ነጥብ አምስት ቢሊየን ብር ወጪ የተገነባው ሪዞርት፤ ሁለት ዓመት ከስድስት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግንባታው ተጠናቆ ለምረቃ መብቃቱ ታውቋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት እየተገነቡ የሚገኙት የቱሪዝም መዳረሻዎች የክልሉን ውበት ከመግለጽ ባለፈ፣ እስካሁን በበቂ ሁኔታ ያልታወቁ ጸጋዎችን ይፋ እያደረጉ ይገኛሉ። ቀደም ሲል የተገነባው የጎርጎራ ፕሮጀክት፣ ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት እና ሌሎች ግንባታዎች የክልሉን ውበትና የኢትዮጵያን የብልጽግና ከፍታ የሚያሳዩ ተጨባጭ ማስረጃዎች መሆናቸውንም ገልጸዋል።   አዲሱ ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት የጣና ሐይቅን ደህንነት በጠበቀ መልኩ የተገነባ፣ የጥራትና የምቾት መለኪያ ተደርጎ የሚወሰድ መሆኑን አመልክተዋል። ሪዞርቱ በታላቁ ወንዝ ስም የተሰየመ የጎብኚዎች መዳረሻ መሆኑን አመልክተው፤ ክልሉ ከቱሪዝም ዘርፍ ተገቢውን ጥቅም እንዲያገኝ ያስችላል ብለዋል። ፕሮጀክቱ በመንግሥትና በግለሰቦች በጋራ የመሥራት ባህል የተገኘ ውጤት መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህም አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎች ግንባታ እውን እየሆነ መሆኑንና በቀጣይም መሰል የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። ለትውልድ የሚተርፉና ሀገርን የሚያስከብሩ ሥራዎች መሥራታችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል።
የገበታ ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያውያን በላባችን ሀገር መገንባት እንደምንችል ማሳያ ናቸው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 3, 2026 132
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የገበታ ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያውያን በላባችን ሀገር መገንባት እንደምንችል ማሳያ ናቸው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በገበታ ለሀገር ኢኒሼቲቭ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትን መነሻ በማድረግ በባህር ዳር ከተማ ጣና ዳርቻ በባለሀብቱ ካሳሁን ምስጋናው የተገነባውን ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ዛሬ መርቀው ከፍተዋል። በመርኃ ግብሩ ላይ የአማራ ክልልና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ አባ ገዳዎች፣ ባለሀብቶችና የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች ተገኝተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፤ የሪዞርቱ መገንባት ለክልሉና ለሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል የቱሪዝም ዘርፍ መጠናከር ተጨማሪ አቅም እንደሆነ ገልጸዋል። በጎርጎራና በፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርቶች መካከል የሚፈጠረው ትስስር ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው የላቀ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ጎብኚዎች ከባህር ዳር ወደ ጎርጎራ፣ ጎንደር፣ ራስ ዳሽን፣ ላሊበላና ትግራይ ክልል የሚያደርጉትን ጉዞ በማቀናጀት የቆይታ ጊዜያቸውን እንዲያራዝሙ ዕድል እንደሚፈጥር አስረድተዋል።   የገበታ ፕሮጀክቶች ዓላማቸው ኢትዮጵያ ያላትን ፀጋና ውበት ገልጣ ለዓለም እንድታሳይ ማድረግ ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህም ግብ አሁን ላይ ፍሬ እያፈራ ነው ብለዋል። አክለውም ኢትዮጵያውያን በደማችን ሀገር መጠበቅ እንደቻልን ሁሉ በላባችንም ሀገር ማልማት እንደምንችል በእነዚህ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች እያሳየን ነው ሲሉ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ባህር ዳር በትልቅ የቱሪዝምና የኢኮኖሚ ልማት ምህዋር ላይ እንደምትገኝ ጠቅሰው፤ የዓባይ አዲሱ ድልድይ በጎንደርና በጎጃም መካከል ያለውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ከማጠናከሩ ባለፈ ራሱን የቻለ የቱሪስት መዳረሻ መሆኑን ገልጸዋል። እየተጠናቀቀ የሚገኘው የባህር ዳር ዓለምአቀፍ ስታዲየም ዓለምአቀፍ ውድድሮችን የማስተናገድ አቅም ባለው ደረጃ መገንባቱን ጠቁመዋል። አዲሱ የአውሮፕላን ማረፊያ ተርሚናል ዓለምአቀፍ በረራዎችንና በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ ለአካባቢው ዕድገት የላቀ መሆኑንም አክለዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገር እና ገበታ ለትውልድ ኢኒሼቲቮች ላይ በንቃት ለተሳተፉ ባለሀብቶች ምስጋና አቅርበዋል። ባህር ዳር ሰላም መሆኗን በመግለጽም፣ ዳያስፖራዎች የወሰዱትን መሬት እንዲያለሙ ጥሪ አቅርበዋል።
የኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ አስደናቂ የሆነ የለውጥ ጉዞ አሳይቷል
May 3, 2026 111
የኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ አስደናቂ የሆነ የለውጥ ጉዞ አሳይቷል። ይህ ጉዞ የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መዋቅር ከግብርና ጥገኝነት ወደ ኢንዱስትሪ በማዞር፣ የውጭ ምንዛሬን በማዳን እና የሥራ ዕድልን በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ‎‎ዘርፉ ከሰነቃቸው ዐበይት ዓላማዎች አንዱ፤ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት በመተካት የንግድ ሚዛኑን ማስተካከል ሲሆን ይህ ጥረት ባለፉት አራት ዓመታት አስደሳች ውጤቶችን አስገኝቷል፦ ‎‎የውጭ ምንዛሬ ገቢ፦ ‎የአምራች ኢንዱስትሪው የወጪ ንግድ በ2014 ከነበረበት 358 ሚሊዮን ዶላር፣ በ2018 በዘጠኝ ወራት ብቻ ወደ 433.8 ሚሊዮን ዶላር ከፍ ብሏል። ይህ ማለት በየዓመቱ ከ5 በመቶ በላይ የሚሆን አማካይ አመታዊ ዕድገት ማስመዝገብ ችሏል። ‎‎የተኪ ምርት ስትራቴጂ፦ ‎መንግሥት 96 ስትራቴጂክ ምርቶችን በመለየት በሀገር ውስጥ እንዲመረቱ በማድረጉ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ማዳን ተችሏል። በዚህም ምርትን በሀገር ውስጥ በመተካት የዳነ የውጭ ምንዛሬ ዕድገት በ2014 በጀት ዓመት ከነበረው 0.343 ቢሊዮን ዶላር፣ በ2018 ዘጠኝ ወራት ውስጥ ወደ 4.85 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል። ‎‎የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪ የገበያ ድርሻ፦ ‎በተመሳሳይ የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎች በገበያው ላይ ያላቸው ድርሻ በከፍተኛ ደረጃ አድጓል፤ በ2014 ከነበረው የ30 በመቶ ድርሻ አሁን ላይ ወደ 46 በመቶ ማደግ ችሏል። ‎‎ኢንቨስትመንት እና የኢንዱስትሪ መስፋፋት፦ ‎ኢንቨስትመንትን ለመሳብ በተደረጉ የህግ ማሻሻያዎች እና የመሠረተ ልማት የማስፋፋት ስራ፣ ዘርፉ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ባለሃብቶችን ቀልብ መሳብ ችሏል። በተለይም ኢትዮጵያ የብሪክስ (BRICS) አባል በመሆኗ እንዲሁም በሌሎች የዲፕሎማሲ ስኬቶች እና የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎች፤ የውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት እንዲስፋፋ አድርገዋል። ‎‎በኢንቨስትመንቱ ስራ፤ ባለፉት አራት ዓመታት ብቻ ከ2,800 በላይ አዳዲስ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንቶች ማሳካት የተቻለ ሲሆን በአማካይ በየዓመቱ ከ700 በላይ ኢንቨስትመንቶች በመሳብ ከፍተኛ ስኬት መመዝገብ ተችሏል። ‎‎የሥራ ዕድል እና ኢንዱስትሪዎች፦ ‎ ከ18,000 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ የገቡ ሲሆን፣ ቀደም ሲል ተዘግተው የነበሩ 993 ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ እንዲመለሱ መደረጉ ለኢኮኖሚው እድገት ከፍተኛ አቅም ፈጥሯል። ‎በአጠቃላይ፣ ይህ እንቅስቃሴ የኢትዮጵያ አምራች ኢንዱስትሪ በገበያ መር የተመሠረተ ዕድገትን እየተቀዳጀ መሆኑንና ቀጣይ መዳረሻው የተሻለ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት መንገድ ላይ መሆኑን በግልጽ ያሳያል። ‎#PMOEthiopia #EthiopiaDelivers #MadeInEthiopia
የኢትዮጵያ አምራቾች ከማምረት ባሻገር የአፍሪካ ገበያን መጠቀም የሚያስችል የንግድ ትስስር መፍጠር አለባቸው
May 3, 2026 118
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አምራቾች ከማምረት ባለፈ የአፍሪካን ገበያ መጠቀም የሚያስችል የንግድ ትስስር መፍጠር እንዳለባቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 25 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ መርቀው ከፍተዋል። ለአራተኛ ጊዜ "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በተዘጋጀው ኤክስፖ ላይ፤ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ቴዎድሮስ ምኅረት፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበልን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ ባለፉት አራት ዓመታት በውጭ ምንዛሬ ከውጭ ይገቡ የነበሩ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በማምረት ረገድ ከፍተኛ ስኬት ተመዝግቧል። አምራቾችና የኢንዱስትሪ ዘርፍ ተዋንያን የኢኮኖሚ አርበኝነትን ሊላበሱ እንደሚገባ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በዚህም ሌብነትና ኮንትሮባንድን በመጸየፍ እውነተኛ የኢኮኖሚ አርበኛ መሆን ያስፈልጋል ብለዋል። የኢትዮጵያ አምራቾች በአገር ውስጥ የማምረት ተግባር ላይ ብቻ ተወስነው የሚቆዩበት ጊዜ አብቅቶ፣ አሁን ወደ አፍሪካ ሰፊ ገበያ የሚገቡበት ወቅት ላይ መሆኑንም ነው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) የገለጹት። እስካሁን “አምርቱ” በሚል ማበረታቻ ሲደረግ የነበረው ጥረት አሁን አምራቾች የአህጉሪቱን የንግድ ዕድሎች ለመቀላቀል እንዲወጡና እንዲሰማሩ ጥሪ አስተላልፈዋል። አምራቾች አቅም ካላቸው በግል፣ ካልሆነም በጋራ በመጣመር አሊያም ከመንግሥት ጋር በመቀናጀት ኩባንያዎችን በመመስረት ወደ አፍሪካ አገራት ዘልቆ መግባት አገራዊ ግዴታቸው ሊሆን እንደሚገባም አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በራሷ ትልቅ ገበያ ያላት አገር መሆኗን ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በአፍሪካ ደረጃ ያለውን ሰፊ የንግድ ዕድል ለመጠቀም አምራቾች ከማምረት ባለፈ ገበያውን ለመቆጣጠር መዘጋጀት እንዳለባቸው ተናግረዋል። አንዱ አምራች እዚህ እያመረተ ሌላው ደግሞ በውጭ አገራት እያከፋፈለ የአፍሪካን የንግድ ሰንሰለት መቆጣጠር ለነገ የማይባል የቤት ሥራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህ ትልቅ ራዕይ ከግብ እንዲደርስም መንግሥት ለዘርፉ ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠርና አስፈላጊ የሆኑ ድጋፎችን ለማድረግ የራሱን የቤት ሥራ በአግባቡ እንደሚወጣ አረጋግጠዋል።   በሀገር ውስጥ በማምረት 96 የምርት ዓይነቶችን መተካት እንደሚቻል መለየቱን ጠቁመው፤ እነዚህን የኢንዱስትሪ ባለሀብቶች የምርት ዓይነቶች በማወቅና በአገር ውስጥ በማምረት ከውጭ እንዳይገቡ ማድረግ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። በቅርቡም የኢትዮጵያን ፍላጎት ሙሉ በሙሉ መሸፈን የሚያስችል የሴራሚክ ፋብሪካዎች ለምረቃ እንደሚበቁ አስታውቀው፤በዚህም በማምረት ክብራችንን፣ ነጻነታችንን እና እድገታችንን ማፋጠን እንችላለን ሲሉ ገልፀዋል። ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት የ10 ነጥብ 2 በመቶ እድገት እንደምታስመዘግብ ገልጸው፤ በግብርና፣ በማዕድን፣ በኢንዱስትሪ፣ በቱሪዝም እና ከሁሉም በላይ በቴክኖሎጂ ዘርፎች አስደናቂ የሆነ ፈጣን እድገት ላይ መሆኗን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በርካታ ምርቶችን ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ገበያም ማቅረብ እየቻለች መሆኗን ገልጸዋል። ለአብነት በመከላከያ ምርቶች ረገድም ቀደም ሲል ከውጭ ይገቡ የነበሩ በርካታ የምርት ዓይነቶችን በአገር ውስጥ ከመተካት ባሻገር ከስድስት በላይ ለሚሆኑ የአፍሪካ ሀገራት ምርቶችን መሸጥ መጀመሩን ተናግረዋል። በመከላከያ፣በልብስ እና በመድኃኒት ምርቶች ራስን መቻል ብቻ ሳይሆን፤ እነዚህን ማምረት የሚያስችሉ ማሽነሪዎችን ጭምር ማምረትና መሸጥ ስንጀምር ሀገራችን በተሟላ ቁመና ላይ ትገኛለች ሲሉ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም