ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በደቡብ ወሎ ዞን በተያዘው የመኸር እርሻ ከ224 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ ይለማል
Jun 28, 2026 530
ደሴ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):-በደቡብ ወሎ ዞን በምግብ ራስን ለመቻልና የኢንዱስትሪ ግብአት አቅርቦትን ለማሳደግ በመኸር እርሻ ከ224 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ እንደሚለማ የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ይመር ሰይድ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ዞኑ ለስንዴ ሰብል ልማት ምቹ በመሆኑ በተያዘው የመኸር እርሻ ስንዴን በስፋት ለማልማት ዝግጅት ተደርጓል። በዚህም በክረምቱ ከ224 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ በማልማት ከ9 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል ብለዋል።   የስንዴ ልማት ምርታማነትን ለማሳደግም ከ400 ሺህ ኩንታል በላይ ሰው ሰራሽ ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑንም ገልጸዋል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ለስንዴ ልማት የተሰጠው ትኩረት አርሶ አደሩን ውጤታማ ከማድረግ ባለፈ በምግብ ራሱን ለመቻልና ለኢንዱስትሪ የሚሆን ግብአት እንዲያቀርብ ማስቻሉንም ተናግረዋል። ስንዴን በሜካናይዜሽን፣ በኩታ ገጠም እና በአዳዲስ አሰራሮች ታግዞ ማምረት መቻሉ እየተገኘ ላለው ውጤት መሰረት መሆኑንም አመልክተዋል። በዞኑ ጀማ ወረዳ የቀበሌ 08 ነዋሪ አርሶ አደር እንድሪስ አበበ በሰጡት አስተያየት እንዳሉት፣ ሁለት ሄክታር መሬታቸውን በስንዴ ለማልማት ማሳቸውን ደጋግመው በማረስ ለዘር ሥራ አዘጋጅተዋል። በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ ታግዘው በማልማትና የሰብል እንክብካቤ ሥራ በማከናወን እስከ 90 ኩንታል ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውንም ገልጸዋል። በዘንድሮው የመኸር ወቅት አንድ ሄክታር ተኩል ማሳቸው ላይ ስንዴ ለማልማት እንደተዘጋጁ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በወረኢሉ ወረዳ የቀበሌ 04 ነዋሪ አርሶ አደር አህመድ ታደሰ ናቸው። ቀደም ሲል ለስንዴ ልማት ብዙም ትኩረት እንደማይሰጡ አስታውሰው፣ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ስንዴን ማልማት ባህል በማድረጋቸው ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። ባለፈው ዓመት በመኸር ወቅት በስንዴ ከለማው 200 ሺህ ሄክታር መሬት ከ6 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን ለማወቅ ተችሏል።
በኦሮሚያ ክልል ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል
Jun 28, 2026 488
አዳማ ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):-በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ በተከናወኑ የልማትና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴዎች ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል መፍጠር ተችሏል። በኦሮሚያ ክልል ከ3 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገብ የቻሉ 1 ሺህ 195 የሚሆኑ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን ወደ ላቀ የኢንቨስትመንት ደረጃ የማሸጋገር ፕሮግራም በአዳማ ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የጨፌ ኦሮሚያ የከተማ ልማት ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አብዱልቃድር ሁሴን እንደገለጹት፤ ኢንተርፕራይዞቹ ከመንግሥት የተሰጣቸውን ዘርፈ-ብዙ ድጋፎችና ምቹ ፓኬጆችን በአግባቡ ወደ ተግባር በመቀየር ለዚህ ስኬትና የሽግግር ደረጃ በቅተዋል።   የክልሉ መንግሥት ድህነትን ለመቀነስ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዲሁም የስራ አጥነት ችግርን በዘላቂነት ለመቅረፍ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩ ኢንተርፕራይዞች ባስመዘገቧቸው ስኬቶች ሳይዘናጉ፣ ይበልጥ ለላቀ ውጤት ለመብቃት በሚሰማሩበት የኢንቨስትመንት መስክ ላይ ጠንክረው መስራት እንዳለባቸውም አቶ አብዱልቃድር አስገንዝበዋል። የኦሮሚያ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ኤባ ገርባ በበኩላቸው፤ ኢንተርፕራይዞቹ በተሰማሩባቸው የሥራ መስኮች ውጤታማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት ደረጃ መሻገራቸውን ገልጸዋል።   በተጨማሪም በመጠናቀቅ ላይ ባለው የበጀት ዓመት ብቻ ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አዲስ የሥራ ዕድል ማመቻቸት መቻሉን ኃላፊው ይፋ አድርገዋል። ኃላፊው አክለውም፤ ወደ ሥራ ለገቡ ዜጎች ከ40 ቢሊዮን ብር በላይ የብድር አቅርቦት መሰራጨቱንና ከ10 ሺህ በላይ የሊዝ ማሽነሪዎችም ለኢንተርፕራይዞቹ መሰጠታቸውን ጠቅሰዋል።   ለሥራ አጥ ዜጎች ከተፈጠሩት የሥራ ዕድሎች መካከል የጎጆ ኢንዱስትሪ፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ንግድ፣ ግብርና፣ አገልግሎት፣ ግንባታ እንዲሁም የብረታ ብረትና የእንጨት ሥራ በዋናነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ገልጸዋል። በተመሳሳይ በበጀት ዓመቱ ከ200 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የክልሉ ዜጎች የውጭ ሀገር የሥራ ዕድል ማመቻቸት መቻሉን ገልጸዋል። ወደ ሥራ ለገቡ ዜጎች የመሥሪያና መሸጫ ቦታዎች እንዲሁም ማዕከላት መተላለፋቸውን የገለጹት ኢንጂነር ኤባ፤ በዚህም ድህነትን በመቀነስ ረገድ ወሳኝ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።   የአዳማ ከተማ ምክትል ከንቲባ ማቲያስ ሰቦቃ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ በከተማዋ ሥራ አጥነትን ለመቀነስና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ዘርፈ-ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በአዳማ በጎጆ ኢንዱስትሪ፣ በከተማ ግብርና በተለይም በዶሮ እርባታ፣ በወተት ላሞች ማድለብና በሰብል ልማት ዘርፎች ለሺዎች ለሚቆጠሩ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያን ጂኦ-ስትራቴጂክ ተጠቃሚነት ለማስጠበቅ የድንበርና የኤርፖርት ደኅንነቶችን ማዘመን ወሳኝ ጉዳይ ነው 
Jun 28, 2026 770
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያን ጂኦ-ስትራቴጂክ ተጠቃሚነት ለማስጠበቅ የድንበርና የኤርፖርት ደኅንነቶችን ማዘመን ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራልና የኤርፖርትና ድንበር አስተዳደር ትራንስፎርሜሽን ፕሮግራም ዐቢይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ገለጹ። የተቀናጀ የኤርፖርት እና የድንበር አስተዳደር ትራንፎርሜሽን ፕሮግራም ላይ ያተኮረ የምክክርና የግብዓት ማሰባሰቢያ መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል።   የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራልና የኤርፖርትና ድንበር አስተዳደር ትራንስፎርሜሽን ፕሮግራም ዐቢይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን በዚሁ ወቅት፤ የትራንስፎርሜሽን ፕሮግራሙ የኢትዮጵያን የደኅንነት ስጋቶች አስቀድሞ ለመከላከል፣ የሳይበር ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና በዲጂታል ዘመን ኢትዮጵያ ያላትን ተወዳዳሪነት ለማስቀጠል ወሳኝ ነው ብለዋል። ፕሮግራሙም ስጋቶችን በመረጃ አስደግፎ ለማወቅና ለመከላከል እንዲሁም በተቋማት መካከል የመረጃ ልውውጥን በማሳደግ ሽብርተኝነት፣ ሕገ-ወጥ የሰዎች፣ የገንዘብና የመሣሪያ ዝውውርን በጋራ ለመመከት አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ፕሮግራሙ ሀገር በቀል ቴክኖሎጂዎች እንዲለሙ በማድረግ የሳይበር ሉዓላዊነትን በማረጋገጥና አሰራሮች በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) እና በሰለጠነ የሰው ኃይል እንዲደገፉ ግብ የጣለ መሆኑንም አስረድተዋል። ለዚህም ስኬት የተዘጋጀው ፍኖተ-ካርታ የሚያስፈልጉትን የቴክኖሎጂ አቅም፣ የአሠራር ሥርዓቶች ስታንዳርድ፣ የሰው ሀብት፣ የመሠረተ-ልማት አቅርቦት እንዲሁም የሕግና የቁጥጥር ጉዳዮችን ለይቶ ማስቀመጡንም አብራርተዋል።   ፕሮግራሙ የሀገሪቱን የጂኦ-ስትራቴጂክ ቁመና ለማስጠበቅና የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አንዱ ማስፈጸሚያ መሣሪያ እንደሆነ ገልጸዋል። የኢትዮጵያን ጂኦ-ስትራቴጂክ ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ የድንበርና የኤርፖርት ደኅንነቶችን ማዘመን እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። በዚህም ሀገሪቱን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርግ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ፍኖተ-ካርታው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ግቦችን ታሳቢ ያደረገ ሲሆን፣ ሀገሪቱ በቀጣይ ለምታስተናግደው ዓለም አቀፍ ኮንፈረንስ ስኬት ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል። በመድረኩ ላይ ከፍተኛ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የጸጥታ ተቋማት መሪዎች ተገኝተዋል።
የቦንጋ ከተማን እድገትና ልማት በማፋጠን ለነዋሪቿ ምቹ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው 
Jun 28, 2026 424
ቦንጋ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):- የቦንጋ ከተማን ዕድገትና ልማት በማፋጠን ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የካፋ ዞን አስተዳደር አስታወቀ። የከተማ አስተዳደሩ ለቀጣይ አሥር ዓመታት ተግባራዊ የሚያደርገው የቦንጋ ከተማ ስትራክቸራል ማስተር ፕላን ላይ ያተኮረ የሕዝብ ውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   ይህ አዲስ ስትራክቸራል ፕላን የከተማዋን የመሠረተ ልማት አቅርቦት፣ የመኖሪያ ቤት ፍላጎት፣ የአረንጓዴ ስፍራዎችን አጠባበቅ እና የኢንዱስትሪ ቀጠናዎችን በዘመናዊ መንገድ ለመምራት የተነደፈ መሆኑም ተገልጿል። ዕቅዱ በቀጣይ አሥር ዓመታት ከተማዋን በፕላን በመምራት በዘፈቀደ የሚደረጉ ግንባታዎችን ለመግታትና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥ ለመዘርጋት ትልቅ መሠረት ይጥላል ተብሎም ይጠበቃል። በመድረኩ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ፤ የቦንጋ ከተማ ረጅም ዓመታትን ያስቆጠረች እድሜ ጠገብ ከተማ መሆኗን ተናግረዋል። ከተማዋ ታሪኳን በሚመጥን መልኩ ሳታድግ መቆየቷን ያነሱት ዋና አስተዳዳሪው፤ አሁን ላይ መንግሥት ለከተሞች ዕድገት ከሰጠው ልዩ ትኩረት በመነሳት፣ የቦንጋን ዕድገት በማፋጠን ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የከተማዋን ፕላን በአዲስ መልክ ማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፣ ከኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ ጋር ውል በመግባት ሰፊ ጥናትና ምርምር ሲደረግ መቆየቱን ዋና አስተዳዳሪው ገልጸዋል። ፕላኑ ላይ ከዚህ ቀደም የተለያዩ የውይይት መድረኮች ሲደረጉ መቆየታቸውን የገለጹት ዋና አስተዳዳሪው፤ በዛሬው የሕዝብ መድረክ ላይ የሚሳተፉ የኅብረተሰብ ክፍሎችም አስፈላጊውን ሐሳብና አስተያየት በመስጠት ለከተማዋ ዕድገትና ልማት የድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። ቦንጋ ከተማ ደረጃዋን የጠበቀችና ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትሆን በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የቦንጋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተክለአብ ቡሎ(ዶ/ር) የገለጹ ሲሆን፤ አዲሱ ማስተር ፕላንም ለዚህ ስኬት ትልቅ ድርሻ እንደሚኖረው አስታውቀዋል።   አዲሱ ስትራክቸራል ፕላን የአካባቢውን ሥነ-ምህዳር መሠረት ያደረገ መሆኑን የጠቀሱት ከንቲባው፤ ከተማዋን ለልማት፣ ለመኖሪያ ቤት፣ ለንግድና ለኢንቨስትመንት ምቹ ከማድረግ ባለፈ የገቢ አቅሟን የሚያሳድግ መሆኑንም ጠቁመዋል። ከዚህም ባሻገር ፕላኑ ለሕብረተሰቡን የረጅም ጊዜ የመልማት ፍላጎት ምላሽ የሚሰጥ መሆኑን ከንቲባው ገልጸው፤ አሁን እየተካሄደ ያለው ውይይት አስፈላጊ ግብዓቶችን በማካተት ፕላኑ በተሟላ መልኩ እንዲተገበር ከፍተኛ ሚና እንዳለው ተናግረዋል። ለሚቀጥሉት አሥር ዓመታት የሚያገለግለው ይህ አዲስ ፕላን፤ የከተማዋን ነባር 6 ሺህ 300 ሄክታር ስፋት ወደ 15 ሺህ ሄክታር በላይ ያሳደገ መሆኑ በውይይቱ ላይ ተመልክቷል። በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮችና የተለያዩ ህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
በኦሮሚያ ክልል የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ የተጠናከረ የሰብል ጥበቃ ሥራ በቅንጅት እየተከናወነ ይገኛል
Jun 28, 2026 271
አዳማ ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀናጀ የሰብል ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የ2018/19 የምርት ዘመን የሰብልና ፍራፍሬ ጥበቃና እንክብካቤ ላይ ያተኮረ የንቅናቄ መድረክ በአዳማ ከተማ በማካሄድ ላይ ይገኛል።   የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ በሪሶ ፈይሳ በወቅቱ፤ በክልሉ ግብርናውን ለማዘመንና ውጤታማ ለማድረግ የተነደፉት ኢኒሼቲቮች አርሶ አደሩንና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ችለዋል። ለዚህ ስኬት ደግሞ የሰብል ጥበቃና እንክብካቤ፣ የግብዓት አቅርቦት፣ የአፈር ለምነት አጠባበቅ እንዲሁም የባለሙያ ድጋፍ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማበርከታቸውን ምክትል ኃላፊው አንስተዋል። በተጨማሪም የሰብል ልማትን በሽፋንም ሆነ በምርታማነት ዘላቂ ለማድረግ ከግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝም አክለው ገልጸዋል። የሰብል ምርትና ምርታማነትን የሚጎዱ አረም፣ ተባይና በሽታዎችን በአስተማማኝ ሁኔታ ለመቆጣጠር ሳይንሳዊ መንገዶች ተግባራዊ እየተደረጉ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዛሬው የንቅናቄ መድረክም የዘርፉ አመራሮችና በየደረጃው የሚገኙ የሰብል እንክብካቤ ባለሙያዎች ይህንኑ ስኬት በጋራ ለማሳካት እንዲረባረቡ ለማስቻል ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። ከሰብል ጥበቃው በተጨማሪ፣ አሲዳማነታቸው የጨመረና ምርታማነታቸው የቀነሰ መሬቶችን በኖራና በተፈጥሮ ማዳበሪያ በማከም ረገድ ሰፊ ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል።   የቢሮው የሰብል እንክብካቤ ኃላፊ አቶ ደጀኔ ሂርጳ በበኩላቸው፤ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ከግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ምርምር ማዕከላቱ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በሽታን የሚቋቋሙ ዝርያዎችን በምርምር በማፍለቅ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግና ሙያዊ እገዛ የመስጠት ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን ለአብነት ጠቁመዋል። ለዚህም ከዘር በፊት የሚደረግ የማሳ ዝግጅት ላይ ትኩረት የተሰጠ ሲሆን፣ ቡቃያውን ከአረሞች፣ ተባዮችና በሽታዎች ቀድሞ መለየትና መከላከል ላይ በቅንጅት በመስራት ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ በየደረጃው የሚገኙ የዘርፉ አመራሮች፣ ባለሙያዎች እና የግብርና ምርምር ማዕከላት ኃላፊዎች ተሳታፊ ሆነዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአፍሪካ ምርጥ የአየር ጭነት አጓጓዥ አየር መንገድ ሽልማትን አሸነፈ
Jun 28, 2026 296
አዲስ አበባ፤ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአፍሪካ ምርጥ የአየር ጭነት አጓጓዥ አየር መንገድ ሽልማትን አሸንፏል። አየር መንገዱ ሽልማቱን ያገኘው የኢትዮጵያ ካርጎ እና ሎጂስቲክስ አገልግሎት በ2026ቱ የእስያ ጭነት፣ ሎጂስቲክስ እና አቅርቦት ሰንሰለት የሽልማት ስነ ስርዓት ላይ ነው። በዚህም የአፍሪካ ምርጥ የአየር ጭነት አጓጓዥ አየር መንገድ በመባል ተሸላሚ ሆኗል።   የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን በጠበቁ መሰረተ ልማቶች፣ ስልታዊ ጥምረቶች፣እንዲሁም አዳዲስ የሎጂስቲክስ አሰራሮች በመታገዝ ዓለም አቀፍ የሎጂስቲክስ እና የንግድ ግንኙነቶችን በማጠናከር ላይ እንደሚገኝም ገልጿል። አየር መንገዱ የካርጎ ሽልማቱን ያገኘው በዘርፉ ባለድርሻ አካላትና በደንበኞች በተሰጠ ከፍተኛ ድምፅ መሆኑን አመልክቷል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ይህ ስኬት ዕውን እንዲሆን ላስቻሉ አጋሮች፣ደንበኞች እንዲሁም ሰራተኞች ምስጋና አቅርቧል፡፡
ቢሮው ተግባራዊ ያደረጋቸው በቴክኖሎጂ የተደገፉ አዳዲስ አሠራሮች የአገልግሎት አሰጣጡን ከማዘመን ባለፈ የከተማዋን የገቢ አቅም አሳድጓል
Jun 27, 2026 802
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ ገቢዎች ቢሮ ተግባራዊ ያደረጋቸው በቴክኖሎጂ የተደገፉ አዳዲስ አሠራሮች የአገልግሎት አሰጣጡን ከማዘመን ባለፈ የከተማዋን የገቢ አቅም ማሳደጉን አስታወቀ፡፡ ቢሮው ቀደም ሲል ግብር ከፋዮች በአካል በመቅረብና የወረቀት ሰነዶችን በመያዝ ያገኙት የነበረውን አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ ወደ ኦንላይን ሥርዓት ማሸጋገር ችሏል። የአዲስ አበባ ከተማ ገቢዎች ቢሮ የሞደርናይዜሽን ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ መሃመድ አብዱረህማን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ ቢሮው ባለፉት ሁለት ዓመታት በርካታ የሪፎርም ሥራዎችን አከናውኗል። ግብር ከፋዮች በአካል ሳይመጡ በኢሜል እና በተዘረጋው የኦንላይን ሊንክ አገልግሎቱን ማግኘት እንዲችሉ ከፌደራል ገቢዎች ሚኒስቴር ጋር በመቀናጀት የተቀናጀ የልማት ሥርዓት ተዘርግቶ ወደ ተግባር መገባቱን ጠቁመዋል። ይህ አዲስ አሠራር ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው አገልግሎት የሚያገኙበት ምኅዳር የፈጠረ ሲሆን፣ የባለቤትነት ስም ዝውውርን ጨምሮ የተለያዩ የሕግ ተገዥነት አገልግሎቶችን ያካተተ መሆኑን አስረድተዋል። ቢሮው በራሱ አቅም ያለማውን የዕዳ ክትትል ሥርዓት ወደ ተግባር በማስገባቱ በ17ቱም ቅርንጫፎች የሚወሰኑ የዕዳ ውሳኔዎችን በቅርበት ለመከታተልና የሚሰበሰበውን ገቢ ወደ ገንዘብ በመለወጥ ረገድ ከፍተኛ አፈጻጸም ተመዝግቧል። የክሊራንስ አሰጣጥ ሂደቱን ይበልጥ ግልጽ፣ ቀልጣፋና እምነት የሚጣልበት ለማድረግ ባርኮድ ያለው አዲስ የኦንላይን አሠራር ተግባራዊ መደረጉንም ተናግረዋል፡፡ የተዘረጉት የዲጂታል አገልግሎቶች ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው ግብራቸውን እንዲያሳውቁና እንዲከፍሉ በማድረጉ፣ በየወሩ መጨረሻ ላይ በቅርንጫፍ ቢሮዎች ይታይ የነበረውን ከፍተኛ መጨናነቅና የረጅም ጊዜ ጥበቃ ማስቀረት መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡ ቢሮው በቀጣዩ በጀት ዓመትም የደረጃ "ሐ" ግብር ከፋዮችን የሚያስተናግደውን የኢቲ ታክስ (eTax) ሥርዓት ሙሉ ለሙሉ ወደ ዲጂታል በማሸጋገር፣ ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችሉ ማሻሻያዎችን እንደሚተገብር ገልጸዋል። በከፍተኛ ግብር ከፋዮች ቅርንጫፍ የኤሌክትሮኒክስ ታክስ ግብይት ድጋፍና ክትትል የሥራ ሂደት ተወካይ አቶ ሰይድ መሃመድ፤ ለግብር ከፋዮች ስለ አገልግሎቱ አጠቃቀም በቂ ስልጠናና ተከታታይ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።   የቅርንጫፉ የኤሌክትሮኒክስ ታክስ ክፍያ አሰባሰብና ክትትል ቡድን አስተባባሪ ተወካይ አቶ ኢድሪስ መሃመድ በበኩላቸው፣ አዲሱ የዲጂታል ሥርዓት ተቋማዊ አፈጻጸምን ከማሳደግና ሥራዎችን ከማቅለል አንጻር ሰፊ ፋይዳ እንዳለው አብራርተዋል።   የቅርንጫፉ ተገልጋዮችም በአዲሱ አሠራር መደሰታቸውን ገልጸዋል፡፡ አቶ ታምራት አብራሃም በሰጡት አስተያየት አዲሱ የኦንላይን ሥርዓት ረጅም ሰልፍን ያስቀረና ተገልጋዩ በቤቱ ሆኖ ሁሉንም አገልግሎት ማግኘት እንዲችል ያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   አዲሱ አሠራር በሥራቸውና በድርጅታቸው ላይ ዘርፈ-ብዙ ጥቅሞችን እንዳስገኘላቸው የገለጹት ደግሞ አቶ ሙልጌታ ተሻለ ናቸው፡፡ አቶ እስጢፋኖስ ብርሃኔ በበኩላቸው የዲጂታል አሠራሩ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ በማስቻል ይደርስባቸው የነበረውን ከፍተኛ እንግልት ሙሉ በሙሉ ማስቀረቱን ገልጸዋል።        
የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በአቅራቢያችን መኖሩ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ አስችሎናል - ሸማቾች
Jun 27, 2026 519
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በአቅራቢያቸው መኖሩ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት እንዳስቻላቸው ሸማቾች ገለጹ። መንግስት አላስፈላጊ የዋጋ ንረትን ለመከላከልና ገበያውን ለማረጋጋት የተለያዩ የግብይት አማራጮችን በመዘርጋት ሸማቾች መሰረታዊ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ የተለያዩ ተግበራት ማከናወኑ ይታወቃል። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በተለያዩ አካባቢዎች ላይ ሕብረተሰቡ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ በማድረግና ገበያን በማረጋጋት ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑ ይታወቃል። ኢዜአ በተለያዩ በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች የቅዳሜና እሁድ ገበያ ስፍራዎች ላይ በመገኘት ቅኝት አድርጓል።   ሐሳባቸውን ካጋሩን አስተያየት ሰጪዎች መካከል ወይዘሮ ሰናይት ብዙአየው እንዳሉት፤ የቅዳሜና እሁድ ገበያ የተለያዩ ጥራት ያላቸውን ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ የሚያገኙበት ስፍራ ነው። ገበያው የኑሮ ውድነትን ለመቋቋም አቅም ከመፍጠር ባሻገር፣ የተለያዩ ምርቶችን በቀጥታ ማግኘት የሚያስችል በመሆኑ ተመራጭ ነው ብለዋል። በገበያው በርካታ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ መቅረባቸው ለሕብረተሰቡ እፎይታ መስጠቱን ገልጸው ገበያው በአቅራቢያቸው መሆኑ ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል፡፡   አቶ ገዳሙ ይበልጣል እና ወይዘሮ አበበች ጎሽም በበኩላቸው፤ ገበያው ከመደበኛው ገበያ ምርቶችን ከፍተኛ ቅናሽ ያለውና የሕብረተሰቡን ገቢ ታሳቢ ያደረገ በመሆኑ ለእኛ ተመራጭ ነው ብለዋል።   በአቅራቢያቸው መኖሩ የግብይት ሥርዓቱን ቀልጣፋ እና ምቹ እንዳደረገላቸው ጠቅሰው የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳለው ተናግረዋል። በቅዳሜ እና እሁድ ገበያ ላይ በመሳተፍ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን የሚያቀርቡ ነጋዴዎች በበኩላቸው፤ ወደ ገበያው ለሚመጡ ሸማቾች ጥራት ያላቸውን ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል።   ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ ፈቃዱ አሜጋ እና አቶ ተመቸው መቻል በሰጡት አስተያየት፤ ሸማቹ የተሻለ ጥራት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ማድረግ መቸላቻውን ጠቅሰዋል፡፡ በተጨማሪም መንግሥት የንግድ ቦታዎችን በነፃ ከማመቻቸቱ ባሻገር፣ ምርቶችን ከአቅራቢዎች በቀላሉ አግኝተው ለኅብረተሰቡ እንዲያቀርቡ ዕድል መፍጠሩንም ገልጸዋል፡፡ ይህም ምርቶችን በበቂ ሁኔታና በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ ለማቅረብ ትልቅ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ገልጸዋል።   የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሀቢባ ሲራጅ በሰጡት አስተያየትም፤ መንግሰት የኑሮ ውድነትን ጫና ለመቀነስና የህብረተሰቡን ፍላጎት ለማሟላት በርካታ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል፡፡ አስተዳደሩ በከተማዋ ትላልቅ የገበያ ማዕከላትን ከመገንባት ጎን ለጎን የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን የማስፋት ስራ በመስራት በርካቶችን ተጠቃሚ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡ በመካከለኛና ዝቅተኛ ደረጃ ላይ ያሉ ዜጎችን የኑሮ ውድነት ጫና ለማቃለል ከመደበኛው ገበያ የ20 በመቶ ቅናሽ ተደርጎ ምርቶች እየቀረቡ ሲሆን፣ ምርቶች በቀጥታ ከአምራቹ ለሸማቹ እንዲደርሱ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል፡፡    
በክልሉ ህዝቡ ሲያቀርባቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን የፈቱ ፕሮጀክቶች በጥራት ተገንብተው ለአገልግሎት እየበቁ ነው
Jun 27, 2026 370
ሆለታ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ህዝቡ ለረጅም ጊዜ ሲያቀርባቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን የፈቱ ፕሮጀክቶች በፍጥነትና በጥራት ተገንብተው ለአገልግሎት እየበቁ መሆኑን የክልሉ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አወሉ አብዲ አስታወቁ። በሆለታ ከተማ ዛሬ ከ700 ሚሊየን 413 ሺህ ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል።   በከተማው ለአገልግሎት ከበቁ ፕሮጀክቶች መካከል የከተማ አስተዳደሩ ባለ 5 ወለል ህንፃ፣ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የይግባኝ ሰሚ ባህላዊ ፍርድ ቤት፣ የዶሮ እርባታ ክላስተር ማዕከል፣ የኮሪደር ልማት እና የጎጆ ኢንዱስትሪዎች መሆናቸው ተገልጿል። በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አወሉ አብዲ እንደተናገሩት በክልሉ ከለውጡ ወዲህ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡና ለረጅም ጊዜ ሲያቀርባቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን የፈቱ ፕሮጀክቶች በፍጥነትና በጥራት ተገንብተው ለአገልግሎት እየበቁ ነው።   በተለይም ከተሞችን ለኑሮ ምቹ እንዲሁም የምርትና ምርታማነት ማዕከል ማድረግ፣ ቀልጣፋ፣ ፍትሐዊና ጥራት ያለው የመንግሥት አገልግሎት መስጫ ስፍራ እየሆኑ ነው ብለዋል። የሆለታ ከተማ በአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት የምትገኝና ረጅም ዕድሜ ያላት ብትሆንም፣ ቀደም ሲል በሚፈለገው ደረጃ ያልለማች ከተማ ነበረች ብለዋል። ከለውጡ ወዲህ ግን በከተማዋ እየተከናወነ ባለው ሥራ ከተማዋ ለኑሮ ምቹ፣ የምርታማነት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን ገልጸዋል። አዲሱ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ማዕከል ዜጎች የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የመንግሥት ልዩ ልዩ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ እንዲያገኙ የሚያስችል ሲሆን፣ በማዕከሉ የተመደቡ ባለሙያዎችም የተጣለባቸውን አደራ በታማኝነት እንዲወጡ አሳስበዋል። የሆለታ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ እሸቱ በቀለ በበኩላቸው፤ ዛሬ የተመረቁት ፕሮጀክቶች የከተማዋን የልማት ዕቅድ ከማሳካት ባለፉት ዓመታት ከተከናወኑት ሰፊ ሥራዎች መካከል ትልቅ ውጤት ናቸው ብለዋል።   በተለይም በ541 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነባው ባለ አምስት ወለል የከተማ አስተዳደር ሕንፃ የቢሮዎችን እጥረት በመቅረፍና ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የሚነሱ ቅሬታዎችን ለመፍታት ያስችላል ብለዋል። ይህ መዋቅር የአገልግሎት ፈላጊዎችን እንግልት በማስቀረትና አላስፈላጊ ወጪን እንደሚያስቀር አብራርተዋል። ከንቲባው አክለውም እነዚህ ፕሮጀክቶች የሥራ ዕድልን ለማስፋፋትና የማህበረሰቡን ኑሮ ለማሻሻል ጠንካራ መሠረት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ማህበረሰቡ በከፍተኛ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብት የተገነቡትን ንብረቶች በአግባቡ ጠብቆ በመጠቀም ለልማቱ ቀጣይነት የበኩሉን ሚና እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።
በከተማና መሠረተ ልማት ዘርፍ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ተግባራት ተከናውነዋል
Jun 27, 2026 431
አርባ ምንጭ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦ በበጀት ዓመቱ በከተማና መሠረተ ልማት ዘርፍ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ያረጋገጡ አበይት ተግባራት መከናወናቸውን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ አስታወቁ። ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ግምገማን በአርባ ምንጭ ከተማ ማካሄድ ጀምሯል።   ሚኒስትሯ ጫልቱ ሳኒ፤ መንግሥት ለከተሞች ዕድገትና መስፋፋት እንዲሁም ለዜጎች ሕይወት መቃናት በልዩ ትኩረት እየሠራ በመሆኑ፣ ዘመኑ የከተሞች የትንሣኤ ዘመን ነው ብለዋል። በበጀት ዓመቱ በተቋማዊ የማስፈጸም አቅም፣ በሀብት አጠቃቀም እና በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ሰፊ ማሻሻያዎች መደረጋቸውንም ገልጸዋል። ከተሞችን የብልጽግና ተምሳሌት ማድረግ የተቻለ ሲሆን፣ የሥራ ባሕላችንን በመቀየር ተወዳዳሪነትን ማሳደግ ተችሏልም ነው ያሉት። ከዚህም ባለፈ በከተሞች በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎች መሠራታቸውን ገልጸው፤ በቤቶች ልማት ዘርፍም ሰፊ ለውጥ እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል። በቀጣይም ከተሞች ከድህነት፣ ከጉስቁልና፣ ከሥራ አጥነት እና ከመልካም አስተዳደር ችግሮች ወጥተው፣ የተጀመረው የብልጽግና ጉዞ እንዲፋጠን በትኩረት እንደሚሠራ ጠቁመዋል።   የአርባ ምንጭ ከተማ ከንቲባ መስፍን መንዛ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ከተማዋ ባላት የተፈጥሮ ጸጋ ልክ ለማደግ ሩቅ አልማ እየተጋች መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ቱሪዝምን የልሕቀት ማዕከል ባደረገ መልኩ መጠነ ሰፊ ልማቶች እየተከናወኑ ሲሆን፣ የኮሪደር ልማቱም የከተማዋን ተወዳዳሪነትና ውበት ይበልጥ ገልጦ እያሳየ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚሁ የአፈጻጸም ግምገማ መድረክ ላይ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ፣ የፌዴራልና የክልል እንዲሁም የተጠሪ ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
በኦሮሚያ ክልል እየተገነቡ ያሉ የመሰረተ ልማት ተቋማት የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች በተጨባጭ እየመለሱ ነው
Jun 27, 2026 293
አዳማ፣ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፡– በኦሮሚያ ክልል እየተገነቡ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች የህዝቡን የመልማት ጥያቄዎች በተጨባጭ እየመለሱ መሆናቸውን በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ ገለፁ።   የክልሉ መንግስት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት ዘርፈ ብዙ አገልግሎት የሚሰጠው የ'አዳማ ሲቲ አሬና' ወይም የህዝብ አደባባይ ዛሬ በይፋ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።   ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው ይኸው ሁለገብ ማዕከል የህዝባዊ ኩነቶችና ዝግጅቶች ማስተናገጃ ስፍራ፣ ዘመናዊ የዳታ ማዕከል፣ ቤተ-መጻሕፍት እና የካፌቴሪያ አገልግሎቶች፣ የገበያ ማዕከልና የስፖርት መዘውተሪያ ስፍራዎች፣ ሰፊ የመኪና ማቆሚያ ያለው መሆኑ ተመልክቷል። በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ፣ ባለፉት አምስት ዓመታት በክልሉ በርካታ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለህዝብ አገልግሎት በቅተዋል። በመጠናቀቅ ላይ ባለው በዚህ በጀት ዓመት ብቻ ከ28 ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች በሁለት ምዕራፎች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን ጠቁመዋል። ዛሬ የተመረቀው የአዳማ ከተማ የህዝብ አደባባይ የ'ስማርት አዳማ' ግቦችን ለማሳካት ከማገዙ ባለፈ፣ በአገልግሎት አሰጣጥና በመልካም አስተዳደር ረገድ የሚታዩ ችግሮችን በዘላቂነት ለመቅረፍ ይረዳል ብለዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት ለአገልግሎት የበቁ የመሰረተ ልማት ተቋማት በተጨባጭ ህዝቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻላቸውን ገልጸው፣ በቀጣይም ስራ አጥነትና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመቀነስ የተጀመሩ ስራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። የክልሉ ነዋሪም በየአካባቢው ለተገነቡ ፕሮጀክቶች ተገቢው ክትትልና እንክብካቤ ሊያደርግላቸው እንደሚገባ አስገንዝበዋል።   የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው፣ የልማት ፕሮጀክቶቹ ለህዝብ የገባነውን ቃል በተግባር ያረጋገጥንባቸውና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እውን ያደረጉ ናቸው ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በከተማዋ የተከናወኑ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውንም ገልጸዋል።   ከተማዋን የኢንዱስትሪ ማዕከል ለማድረግና ስራ አጥነትን ለመቀነስ በተከናወኑ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። በተለይም የኮሪደር ልማት ስራዎች መሳካታቸውን፣ የመንግስት አገልግሎትና የሀብት አስተዳደር ሥርዓት መዘመኑን፣ የመሬት ሀብት አስተዳደር ከውስብስብ ችግሮች ወጥቶ ለልማት አጋዥ መሆኑን ጠቅሰዋል። ይህ የአሰራር ማዘመን ሂደት የከተማዋን ገቢ ከማሳደጉም በላይ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎችን በራስ አቅም ለመሸፈን ትልቅ አቅም መፍጠሩን አቶ ኃይሉ አብራርተዋል።
የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጡ መሆኑን አመላካች ናቸው
Jun 26, 2026 1164
አዲስ አበባ፤ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጡ እንደሚገኙ አመላካች መሆናቸውን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ። የገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ በበኩላቸው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ዘመናዊ የኢኮኖሚ አስተዳደር ሥርዓትን በመገንባት ረገድ ገንቢ ሚና ማበርከቱን ተናግረዋል። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 1ኛ ልዩ ስብሰባ በዛሬው ዕለት ተካሂዷል። ምክር ቤቱ ባካሄደው ልዩ ስብሰባ ከዓለም አቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተፈረሙ ሦስት የፋይናንስ ድጋፍና ብድር ስምምነት አዋጆችን አጽድቋል፡፡ የገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ባለፉት ዓመታት የተተገበረው የተሟላ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የፋይናንስ ዘርፉን በማረጋጋት ረገድ አወንታዊ ሚና አበርክቷል፡፡ በተለይ ደግሞ የገቢ አሰባሰብንና የውጭ ምንዛሬ መጠንን በከፍተኛ መጠን ማሳደጉን ተናግረዋል፡፡ ሪፎርሙ ዘመናዊ የኢኮኖሚ አስተዳደር ሥርዓትን በመገንባት ረገድ ገንቢ ሚና መጫወቱንም ነው የገለጹት፡፡ ከዓለም አቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተፈረሙ የድጋፍና ብድር ስምምነቶች በፋይናንስ፣ በንግድ፣ በአየር ንብረት ለውጥ፣ በኢነርጂ፣ በመሠረተ ልማት፣ በግብርና እና በሌሎች ዘርፎች እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን ለመደገፍ የሚውሉ ናቸው ብለዋል፡፡ የወጣቶችን፣ ሴቶችን፣ የአርሶና አርብቶ አደሮችን ሕይወት ለማሻሻል በሚደረገው ርብርብ ትልቅ የፋይናንስ አቅም እንደሚፈጥሩም ጠቁመዋል። የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባትና የመስኖ ልማቶችን ለማዘመን እንደሚያግዙም እንዲሁ። የምክር ቤት አባላት በበኩላቸው፤ የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ምን ያህል ለውጥ እያመጡና የሕብረተሰቡን ሕይወት በተጨባጭ እየቀየሩ በመሆኑ የተገኙ ናቸው ብለዋል። ለተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች መሳካትም ትልቅ የፋይናንስ አቅም እንደሚሆኑ ተናግረዋል፡፡ ምክር ቤቱ በልዩ ስብሰባው ከጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የቀረበለትን ሪፖርት መርምሮ የምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብ አዋጅን አጽድቋል፡፡ በተመሳሳይ ከግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የቀረበለትን የግብርና ቢዝነስ ካምፓኒ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ አጽድቋል፡፡ #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ኢትዮጵያ ቀጣናዊ መሰረተ ልማቶችን በመገንባት አህጉራዊ ኃላፊነቷን በብቃት እየተወጣች ነው
Jun 26, 2026 744
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያሳልጡ ወሳኝ መሰረተ ልማቶችን በመገንባት አህጉራዊ ኃላፊነቷን በብቃት እየተወጣች መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ ገለጹ። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ከአፍሪካ ሀገራት ጋር ያላቸውን የኢኮኖሚ፣ የኢንቨስትመንትና የጂኦፖለቲካዊ ትስስር ይበልጥ ለማሳደግ ያለመ "ሂሊ ዲያሎግ-አፍሪካ ኤዲሽን" የምክክር መድረክ ተካሂዷል።   የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ በመድረኩ፤ ኢትዮጵያ ቀጣናዊ ትስስርን የሚያሳልጡ መሰረተ ልማቶችን በመገንባት ውጤታማ ስራ እያከናወነች ነው ብለዋል። በዚህም የምስራቅ አፍሪካ ሀገራትን በኤሌክትሪክ ኃይል፣ በመንገድና በመሳሰሉት መሰረተ ልማቶች በማስተሳሰር የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያሳልጥ ገንቢ ሚና እየተወጣች መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እስከ ታንዛኒያ ድረስ የኤሌክትሪክ መስመር በመዘርጋት የምትሰራው ውጤታማ የልማት ሥራም አህጉራዊ ኃላፊነቷን በብቃት እየተወጣች መሆኗን እንደሚያሳይ ተናግረዋል። የአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063ን ዕውን ለማድረግም አባል ሀገራት የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያሳልጡ መሰረተ ልማቶችን መዘርጋት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊና ቀጣናዊ የመሰረተ ልማት ውጤቶችም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ሀገራዊ ዕድገትን የሚያፋጥኑ መሆናቸውን አስረድተዋል። ለዲጂታል ኢኮኖሚ የተሰጠው ትኩረትም ንግድና ኢንቨስትመንትን በማሳለጥ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ባለሃብቶች ጨምሮ ለውጭ አልሚዎች አስቻይ ምኅዳር መፍጠሩን አስረድተዋል። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የስትራቴጂክ ጥናትና ምርምር ማዕከል ኢኮኖሚስትና ተመራማሪ መሐመድ አል አባቢ በበኩላቸው፤ አፍሪካ በሁሉም መስክ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ስትራቴጂክ አጋር ናት ብለዋል። በዚህም በምግብ ዋስትና፣ በታዳሽ ኃይልና ቁልፍ መሰረተ ልማት ግንባታ ዘርፍ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ትብብር በመፍጠር እየሰራች እንደምትገኝ ገልጸዋል።
በካፋ ዞን በዘንድሮ የመኸር እርሻ ከ126 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይለማል
Jun 26, 2026 314
ቦንጋ ፤ ሰኔ 19 /2018 (ኢዜአ)፦ በካፋ ዞን በዘንድሮ የመኸር አዝመራ ከ126 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት እንደሚለማ የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለፀ። የዞኑ ግብርና መምሪያ የ2018 ዓመተ ምህረት የግብርና ተግባራት አፈጻጸም ግምገማና የ2018/19 የመኸር ግብርና ስራዎች ዕቅድ ንቅናቄ መድረክ አካሄዷል። በመድረኩ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ ለግብርናው ዘርፍ የተሰጠውን ትኩረት በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ይበልጥ ለማሳደግ ርብርብ ይደረጋል ብለዋል።   ግብርና ሁሉን አቀፍ ለውጥ ለማስመዝገብ ወሳኝ ዘርፍ በመሆኑ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግና ዘመናዊ አሰራሮችን በመከተል ያለውን አቅም አስተባብሮ ወደ ስራ በመግባት የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ ይገባል ብለዋል። በዘንድሮው የመኸር እርሻ 126 ሺህ 491 ሄክታር መሬት ለማልማት መታቀዱን ገልፀዋል። በዚህም የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት በየደረጃው በቁርጠኝነት ይሰራል ያሉት አስተዳዳሪው፣ ለአረንጓዴ አሻራ፣ ለቡና ልማትና ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ልዩ ትኩረት ይሰጣል ነው ያሉት። የካፋ ዞን ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ሥራ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ገረመው ገብሬ በበኩላቸው በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ3 ሚሊዮን 225 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።   ለዚህም የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን 40 በመቶ በማድረስና 30 በመቶ የሚሆነውን መሬት በክላስቴር በማልማት የታቀደውን ያህል ምርት ለማምረት ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። የግብዓት እጥረት እንዳይገጥም የተፈጥሮ ማዳበሪያ አጠቃቀም ላይ ትኩረት እንደሚሰጥ ያነሱት አቶ ገረመው የማይታረስ መሬትን ዜሮ በማድረስ የተያዘውን እቅድ ለማሳካት የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። በዘንድሮው የመኸር አዝመራ የተያዘውን እቅድ ለማሳካት ቴክኖሎጂን ከመጠቀም ባለፈ ለኩታ ገጠም እርሻ ትኩረት በመስጠት ምርታማነትን ለማሳደግ እንደሚሰሩ የገለፁት ደግሞ የጠሎና ወረዳ ዋና አስተዳደሪ አቶ አትርሴ ሸታቸው እና የሺሾ እንዴ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ደምሴ ገብረማርያም ናቸው። በ2017/18 የመኸር አዝመራ ከ123 ሺህ ሄክታር በላይ መሬትን በማልማት ከ2 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡንም ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው ልዩ ስብሰባ የተለያዩ የብድርና ድጋፍ ስምምነት አዋጆችን አጸደቀ
Jun 26, 2026 360
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው ልዩ ስብሰባ ከዓለም ዓቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተፈረሙ ሶስት የፋይናንስ ድጋፍና ብድር ስምምነት አዋጆችን አጸደቀ፡፡ 6ኛው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 1ኛ ልዩ ስብሰባ በዛሬው እለት ተካሂዷል።   ለምክር ቤቱ ከቀረቡት ስምምነቶች መካከል የመጀመሪያው ለዘላቂ እና ሁሉን አቀፍ የእድገት ልማት ፖሊሲ ማስፈፀሚያ የሚውል የአራት መቶ ሰላሳ ሰባት ሚሊዮን አራት መቶ ሺ (437,400,000) ኤስ.ዲ.አር የብድር ስምምነት ነው፡፡ ሁለተኛው የማህበረሰብ ተኮር የመሬት አያያዝ ፕሮግራም ማስፈፀሚያ የሚውል የአንድ መቶ አርባ አምስት ሚሊዮን አምስት መቶ ሺ (145,500,000) ኤስ.ዲ.አር የብድር ስምምነት ነው፡፡ ሶስተኛው ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የመስኖ ልማት ለዘላቂ ምርታማነት ፕሮጀክት ማስፈፀሚያ የሀምሳ አራት ሚሊዮን ስድስት መቶ ሺ (54,600,000) ኤስ.ዲ.አር የብድር ስምምነት ነው፡፡ ምክር ቤቱም እነኚህን የብድርና ድጋፍ ስምምነት አዋጆችን መርምሮ አጽድቋል።   የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ በዚሁ ወቅት፤ የብድርና ድጋፍ ስምምነቶች ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ምን ያክል ለውጥ እያመጡ እና የህብረተሰቡን ህይወት በተጨባጭ እየቀየሩ መሆናቸውን የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙን ይበልጥ በማጠናከር፤ ወደ ውጪ የሚላኩ ምርቶችን በመጠንና በጥራት በማሳደግ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት አይነተኛ ሚና እንደሚኖራቸው ገልጸዋል። የወጣቶችን፣ ሴቶችን፣ የአርሶና አርብቶ አደሮችን ህይወት ለማሻሻል በሚደረገው ረብርብ ትልቅ የፋይናንስ አቅም እንደሚሆን ጠቁመዋል። የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባትና የመስኖ ልማቶችን ለማዘመን እንደሚያግዝም እንዲሁ።
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች ነው
Jun 26, 2026 233
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች መሆኑ ተገለጸ፡፡ የመንገድ ደህንነት መድን ፈንድ አገልግሎት በመንገድ ትራፊክ አደጋ የሚደርሰውን ሞት ፣ የአካል ጉዳትና የንብረት ውድመት ለመቀነስ በዘርፉ የተቀመጡ ሀገራዊና ዓለም አቀፋዊ ግቦችን ለማሳካት የግማሽ ዘመን ስትራቴጂ አፈፃፀም ላይ ሀገር አቀፍ ጉባኤ እያካሄደ ይገኛል።   የኢትዮጵያ የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አባሶ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ ደህንነቱ የተጠበቀ የትራፊክ ፍሰት ለመፍጠር የተጀመሩ የስትራቴጂክ ስራዎች ተጨባጭ ፍሬ ማፍራት ጀምረዋል፡፡ አገልግሎቱ የትራፊክ አደጋ ስጋትን ለመቀነስ በቅንጅት ያከናወናቸው ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤት እያስገኙ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ በተከናወኑት ስልታዊ የቅድመ-መከላከል ስራዎች ምክንያት የአደጋው ቁጥር ጉልህ መሻሻል እያሳየ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ የወርልድ ሪሶርስ ኢንስቲትዩት (WRI) ከፍተኛ ባለሙያ ኢንጂነር ሰመረ ጅላሉ በበኩላቸው፤ ከ2021 እስከ 2030 የተቀመጡትን ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦች ለማሳካት በርካታ ስኬታማ ተግባራት ማከናወኗን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች መሆኗን ገልጸዋል፡፡ በሕብረተሰቡ ዘንድ በትራፊክ አደጋ ተጋላጭነት ዙሪያ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች ሲከናወኑ የቆዩ ሲሆን፣ በቀጣይም ተግባራቱ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በመድረኩ ተጠቅሷል፡፡ በዚሁ ሀገር አቀፍ ጉባኤ ላይ የኢትዮጵያ የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት በዲጂታል የታገዘ የትራፊክ አደጋ መረጃ አስተዳደር ሥርዓት ለኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አስረክቧል፡፡  
የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርምን በላቀ የአመራር ጥበብ ለመፈፀም በትኩረት እየተሰራ ነው- አቶ አረጋ ከበደ
Jun 26, 2026 216
ባሕር ዳር፤ ሰኔ 19/2018(ኢዜአ)፡- በተቋማት እየተካሄደ የሚገኘውን የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም በላቀ የአመራር ጥበብ በመፈፀም የመልካም አስተዳደር ችግርን ለመቅረፍ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለፁ። በአማራ ክልል በመጀመሪያው ዙር ወደ መንግሥት አገልግሎት እና አሥተዳደር ሪፎርም የሚገቡ ተቋማትን የቅድመ ዝግጅት ሁኔታ በተመለከተ በባሕር ዳር ከተማ እየተገመገመ ነው።   ርእሰ መስተዳድሩ አቶ አረጋ ከበደ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ መንግስት የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርምን በመቅረጽ የክልሉ ህዝብ የሚያነሳውን የመልካም አስተዳደር ችግር ለመቅረፍ እየሰራ ነው፡፡ በዚህም ለህዝቡ ፈጣን፣ ፍትሃዊና እርካታን የፈጠረ አገልግሎት ለመስጠት በቁርጠኝነት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥም በከተሞች መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግና በተቋማት የመንግስት አገልግሎት አስተዳደር ሪፎርምን በመተግበር ውጤታማ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በምክትል ርእሰ መስተዳድር ማእረግ የከተማ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የሪፎርሙ ስትሪንግ ኮሚቴ ሰብሳቢ አህመዲን መሃመድ (ዶ/ር) በበኩላቸው ሪፎርሙ የተቀናጀ መዋቅር፣ በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራርና ቁርጠኛ አመራርን የሚጠይቅ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ሪፎርሙን በክልል ደረጃ በተሟላ መልኩ በመተግበር ወደ ታች ለማውረድ እየተሰራ እንደሚገኝም ነው ያመለከቱት። የዛሬው መድረክ ዋና ዓላማም ቀድመው ሪፎርሙን ተግባራዊ ያደረጉ ተቋማት አተገባበር ያለበትን ሁኔታ በመገምገም በቀጣይ የላቀ አፈጻጸም ለማስመዝገብ ያለመ ነው ብለዋል። የአማራ ክልል የሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ባንችአምላክ ገብረማርያም እንደገለጹት፤ ባለፉት ሶስት ወራት በስምንት ተቋማት የተጀመረውን የሪፎርም ትግበራን ለማስፋት እየተሰራ ነው። ተቋማቱ በዝግጅት ምእራፍ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ማስፈጸሚያ መመሪያ በማዘጋጀትና የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት መስክ ያከናወኑት ተግባር አበረታች መሆኑን ገልጸዋል። ይህም ከሀምሌ ወር 2018 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ሪፎርም ትግበራው ለሚገቡ ተጨማሪ ዘጠኝ ተቋማት ልምድና ተሞክሮ ለማስተላለፍ እንደሚያስችል አስገንዝበዋል። በመጀመሪያው ምእራፍ የሪፎርም ትግበራ ግብርና ፣ ጤና ፣ ትምህርት፣ ስራና ክህሎት፣ ሲቪል ሰርቪስ ፣ ገንዘብ ፣ ገቢዎችና ፕላን ልማት ቢሮዎች መካተታቸው የሚታወስ ነው።  
ማዕድን ዘርፍ- በሀገራዊ ለውጡ ያንሰራራው የኢትዮጵያ አቅም
Jun 26, 2026 277
በሙሴ መለሰ የኢትዮጵያ የማዕድን ዘርፍ በአገር በቀል የኢኮኖሚና የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ታግዞ፣ ባለፉት ዓመታት የታዩበትን የአሰራርና መዋቅራዊ ችግሮች በመቀረፍ ከፍተኛ የመነቃቃት ምዕራፍ ላይ ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአንድ ወቅት እንደገለጹት፣ ማዕድን በብዝኃ ዘርፍ የልማት ምልከታችን ውስጥ እና በአገሪቱ የሰላሳ ዓመታት የልማት ዕቅድ ውስጥ ትኩረት ከተሰጣቸው አምስት የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ ቁልፍ ዘርፍ ሆኖ ይቀጥላል። መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው የላቀ ትኩረትና ባከናወናቸው የማስተዋወቅ ሥራዎች፣ የማዕድን ልማት በአሁኑ ወቅት የሀገሪቱ የኢኮኖሚ ጀርባ አጥንት ወደ መሆን ተሸጋግሯል። ባለፉት ሦስት አሥርት ዓመታት ውስጥ የማዕድን ዘርፉ ለአጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) ያበረከተው አስተዋጽኦ ከዜሮ ነጥብ ስምንት በመቶ በታች የነበረ ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት ግን አስገራሚ መዋቅራዊ ሽግግር እየተመዘገበ ይገኛል። በቅርብ የወጡ የቁጥር መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፣ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያዎቹ ዘጠኝ ወራት ብቻ ዘርፉ ወደ አራት ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ገቢ በማስመዝገብ የአገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ውስጥ ያለውን ድርሻ በከፍተኛ ሁኔታ አሳድጓል። ይህም ከቀዳሚው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ92 በመቶ የገቢ ዕድገትና የ27 በመቶ የምርት መጠን ብልጫ ማሳየቱን ያረጋግጣል። ምርቶቹ በከፍተኛ ደረጃ የሚላኩትም ወደ ሳውዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ አሜሪካ፣ ጀርመን እና ቻይና የመሳሰሉ ግዙፍ የዓለም ገበያዎች ነው። በዚህ ታሪካዊ ስኬት ውስጥ የወርቅ ምርት የወጪ ንግድ ዘርፉ ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚመመዘገብ ማዕድን አይነት ነው። የወርቅ ወጪ ንግድ በያዝነው ዓመት ከአምስት ነጥብ አምስት ቢሊዮን ዶላር በላይ ያስገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ የማዕድን ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ይህም እንደ ከፍተኛ እምርታ ነው ማለት ይቻላል። በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያዎቹ ስምንት ወራት ብቻ 22 ነጥብ 5 ቶን ወርቅ ለውጭ ገበያ የቀረበ ሲሆን፣ እስከ ዓመቱ ማብቂያ ድረስ መጠኑ 32 ቶን ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል። በአሁኑ ወቅት የወርቅ ምርቱ 95 በመቶ የሚሆነው በባህላዊ አምራቾች ዘዴ የሚመረት ቢሆንም፣ ይህንን አሠራር ይበልጥ ዘመናዊና ውጤታማ ለማድረግ መንግሥት አነስተኛ የወርቅ ማጣሪያና ማቅለጫ ፋብሪካዎችን ለመገንባት በከፍተኛ ትኩረት እየሰራ ነው። የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት በጽኑ መሠረት ላይ ለማቆም ከውጭ የሚገቡ ስትራቴጂክ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት የመተካት ሰፊ ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛል። በዚህም መሠረት በየዓመቱ ለከሰል ምርት ግዢ ይወጣ የነበረውን 300 ሚሊዮን ዶላር ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ ምርት መተካት የተቻለ ሲሆን፣ የሲሚንቶ ምርትም ባለፉት ስምንት ዓመታት ከነበረበት ስምንት ሚሊዮን ቶን አሁን ላይ በዓመት ወደ 14 ሚሊዮን ቶን ምርቱ እንዲያድግ ተደርጓል። በተመሳሳይ መልኩ አገሪቱ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የምታስገባውን የተፈጥሮ ጋዝ በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ በሀገር ውስጥ የማምረት እንቅስቃሴ ተጀምሯል። ይህም ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የጉባ ብስራቶች መካከል አንዱ ነው። ይህንን ተከትሎም በአዲስ አበባ-ጂቡቲ ኮሪደር ላይ ሦስት የጋዝ መሙያ ማደያዎች የተገነቡ ሲሆን፣ ከ1 ሺህ 500 በላይ የከተማ አውቶቡሶችን ከናፍጣ ነዳጅ ወደ ጋዝ የመቀየር የሽግግር ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ሚኒስቴሩ ገልጿል። በሌላ በኩል የብሔራዊ ኢኮኖሚው ምሰሶ የሆነውን የግብርና ዘርፍና የኢንዱስትሪ ግብዓቶችን ለማጠናከር ግዙፍ ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ወደ ሥራ ገብተዋል። ለ34 ሚሊዮን ያህል አርሶ አደሮች ፍላጎት ማሟያ በየዓመቱ ለማዳበሪያ ግዢ የሚወጣውን ሁለት ቢሊዮን ዶላር ለማስቀረት፣ መንግሥት የማዳበሪያ ፋብሪካ በሚቀጥሉት 29 እስከ 30 ወራት ውስጥ ተጠናቆ ወደ ሥራ እንዲገባ እየተሰራ ይገኛል። ይህም ሙሉ በሙሉ የሀገር ውስጥ ፍላጎትን የሚሸፍን ይሆናል። እንዲሁም በየዓመቱ የብረት ምርትን ከውጪ ለማስገባት የሚወጣውን አንድ ቢሊዮን ዶላር በሀገር ውስጥ ምርት ለመተካት የሚያስችል ግዙፍ የፋብሪካ ግንባታ ስምምነት ተፈርሞ ወደ ተግባር ተገብቷል። እንደሚታወቀው የለውጡ መንግስት ከመጣ በኋላ የፕሮጀክቶች መጀመር ብቻ ሳይሆን በተያዘላቸው ጊዜ ማጠናቀቅንም ቀድሞ ታሳቢ ያደርጋል። ለዚህ ደግሞ በቀደመው አሰራር የስምንት ሰዓት እለታዊ ስምሪት ሳይሆን 24 ሰዓታትን በመትጋት ማከናወን የሰርክ ተግባር ነው። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተከትሎ በሀገር ውስጥ እና በወጪ ገበያ ምርት መጠን ላይ ከፍተኛ እድገት እየተመዘገበ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት 10 ቢሊዮን ዶላር የሚገመቱ ግዙፍ ፕሮጀክቶች በማዕድን ዘርፉ ውስጥ ተሰማርተዋል። ይህም ከለውጡ በፊት ከነበረውና ከ100 ሚሊዮን ዶላር የማይበልጡ አነስተኛ ኢንቨስትመንቶች የነበሩበትን አሳሳቢ ሁኔታ በከፍተኛ ደረጃ የለወጠ ስኬት ነው። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ በዓለም ላይ ካሉ ያልተነኩ ግዙፍ የፖታሽ ክምችቶች መካከል አንዱ የሚገኝበትን የአፋር ክልል የማልማት ፈቃድ አግኝቶ ወደ ሥራ ገብቷል። ከዚህ ባለፈም ባለፉት 30 ዓመታት ምንም ዓይነት እሴት ሳይጨምርበት እንዲሁ ይላክ የነበረውን የታንታለም ማዕድን፣ አሁን ላይ በሀገር ውስጥ እሴት ጨምሮ ለዓለም ገበያ ለማቅረብ መንግስት ከአሜሪካ ኩባንያ ጋር ድርድር ላይ ይገኛል። ከወርቅ በተጨማሪ ለዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂና የባትሪ ምርት ወሳኝ የሆኑትን ሊቲየም፣ ኮባልትና ኒኬል የመሳሰሉ ማዕድናትን በስፋት ለማምረት ዝግጅቶች ተጠናቀዋል። የኢንቨስትመንት ምህዳሩን ይበልጥ ሳቢና ፍትሐዊ ለማድረግ የአሰራር ማሻሻያዎች ተተግብረዋል። የማዕድን ፍለጋ እና ምርት ፈቃድ አሰጣጥን ግልጽ ለማድረግ አሠራሩ ቅድሚያ የመጣን ቅድሚያ ማስተናገድ ላይ የተመሠረተ እንዲሆን ተደርጓል። የአገልግሎት አሰጣጡን ለማቀላጠፍም የወጪ ንግድ ኮንትራት ምዝገባ እና የመላኪያ ፈቃድ አገልግሎቶች ሙሉ በሙሉ ወደ ኦንላይን ሥርዓት የተሸጋገሩ ሲሆን፣ አዲስ ፈቃድ ለማውጣት ወይም ለማደስ የኤሌክትሮኒክስ የንግድ ሥርዓት ድረ-ገጽ እና የማዕድን ካዳስተር ሲስተምም ተዘርግቷል። በማዕድን ግብይት አዋጅ መሠረት በዘርፉ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች የማዕድን ላኪነት፣ የሀገር ውስጥ ንግድ፣ የማጣራትና ማቅለጥ እንዲሁም የአቅራቢነትና ዕደ-ጥበብ ፈቃዶች በግልጽና ቀልጣፋ በሆነ መንገድ እንዲሰጡ ተደርጓል። ከዚህ በተጨማሪም በማዕድን ማምረት ሥራዎች የሚገኘው ገቢ የተወሰነ ክፍል ማዕድኑ በሚወጣበት አካባቢ ለሚገኘው ማህበረሰብ ልማት እንዲውል በሕግ ተደንግጎ ወደ ሥራ መተርጎሙ የሕዝብን ተጠቃሚነትም አረጋግጧል። መንግሥት የኮንትሮባንድ ቁጥጥርን በከፍተኛ ደረጃ በማጥበቅና ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን በመቆጣጠር፣ ምርቶች በይፋዊ የገበያ ሰንሰለት ብቻ ለውጭ ገበያ እንዲቀርቡ በማድረግ ፈተናዎቹን በቁርጠኝነት እየመከተ ይገኛል። የማዕድን ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሃና ብርሃኑ ኢትዮጵያ ታከናውናለች በተሰኘው ብሔራዊ ጉባኤ ላይ እንደገለጹት፣ የመንግሥት ስልታዊ እቅድ እ.ኤ.አ. በ2030 የማዕድን ወጪ ንግድ ገቢን ከማዕድን ዘርፍ ከ10 ቢሊዮን ዶላር በላይ ማድረስ ነው። ይህ ታላቅ ራዕይ ኢትዮጵያን ከአፍሪካ አምስት ቀዳሚ የማዕድን አምራች ሀገራት ተርታ ለማሰለፍ ያለመም ነው። መንግስት በማዕድን ዘርፍ ያለውን ይህንን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ በመጠቀም ወደ ላቀ ብልፅግና ለመቀየር በዘርፉ ለሚሰማሩ የሀገር ውስጥና የውጭ ኢንቨስተሮች ሁሉን አቀፍ ድጋፍና ማበረታቻ ለማድረግ ሙሉ በሙሉ ዝግጁ መሆኑን አረጋግጧል።
ከአፍሪካ ትልሞች ጋር የተሳሰረው የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት
Jun 26, 2026 293
ኢትዮጵያ በታሪክ አጋጣሚዎች በአፍሪካ የነጻነት ትግል ግንባር ቀደም በመሆን፣ የቅኝ ግዛት ቀንበርን በመስበር ለቀሪው አህጉር የተስፋ ብርሃን የፈነጠቀች ሀገር ናት። ዛሬም፣ኢትዮጵያ ይህንን ታሪካዊ አደራ በመቀጠል፣ በሜጋ ፕሮጀክቶቿ ስኬት የአፍሪካን የኢኮኖሚ ነጻነትና ትስስር በመምራት ላይ ትገኛለች።እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ፣ የቢሾፍቱ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ የጎዴ የዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካ፣የኦጋዴን ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ ፕሮጀክት እንዲሁም በሌሎች ዘርፎችም ጭምር ከሀገር ስኬት ባሻገር የአህጉሪቱን የልማት ህልም እውን የሚያደርጉ ቁልፍ መሰረተ ልማቶች በመከወን ላይናቸው።   የአፍሪካ የኢኮኖሚ ዕድገት ዋነኛው ማነቆ የኃይል አቅርቦት እጥረት መሆኑ አጠያያቂ አይደለም።ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ፍላጎት ማሟያ ብቻ ሳይሆን፣ለቀጠናው አገራት አስተማማኝ የኃይል ምንጭ በመሆን የአፍሪካን የኢንዱስትሪ ሽግግር የሚያፋጥን የኃይል ማዕከል በመሆን ለቀጣናው የቀረበ ውድ ስጦታ ነው። ይህ ፕሮጀክት አፍሪካ በራሷ ሃብት ተጠቅማ የኃይል ዋስትናዋን ማረጋገጥ እንደምትችል የሚያሳይ በራስ የመተማመን ምልክት ነው።   ኢትዮጵያ በሜጋ ፕሮጀክቶቿ የምትገነባው የሎጂስቲክስ አውታርም፣ ለአፍሪካ የንግድ ትስስር እውን መሆን ወሳኝ ነው።የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ለቀጣዩ የአህጉሪቱ የዕድገት ምዕራፍ የተዘጋጀ ስልታዊ ምላሽ ከመሆኑም በላይ፣ የኢትዮጵያን ብልጽግና ከአፍሪካ ብልጽግና ጋር የሚያቆራኝ ወሳኝ የሜጋ ፕሮጀክት ነው። አፍሪካ በራሷ ጥረት የዓለም አቀፍ ደረጃ መሰረተ ልማቶችን መገንባት እንደምትችል ኢትዮጵያ በእዚህ ፕሮጀክቷ በኩል መልዕክት እያስተላለፈች ነው።ይህ አውሮፕላን ማረፊያ ኢትዮጵያን በአህጉሪቱ የልማት ግንባር ቀደምትነቷን የሚያጸና፣ እንዲሁም የነገውን የአፍሪካ ህልም ወደ ተግባር የሚቀይር የልህቀት ማማ ነው።   የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት ከአፍሪካ የልማት ትልም ጋር የተሳሰረበት ሌላው ቁልፍ ምክንያት አፍሪካ ያለ ውጭ ዕርዳታና ጣልቃ ገብነት፣በራሷ ህዝብ ሃብትና ጥረት ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መገንባት እንደምትችል ኢትዮጵያ በተግባር እያሳየች ነው።ይህ ለሌሎች የአፍሪካ አገራት ታላቅ የልማት ተምሳሌት ነው። የቴክኖሎጂ ሽግግርን፣የባለሙያ አቅም ግንባታን እንዲሁም የፕሮጀክት አመራር ክህሎትን በማጎልበት፣ኢትዮጵያ የአፍሪካን የሰው ሃይል ለለውጥ እያዘጋጀች ስለመሆኑ አያጠራጥርም። የሜጋ ፕሮጀክቶቹ ተፅዕኖ ከኢትዮጵያ ድንበር አልፎ በምስራቅ አፍሪካ ቀጠና ላይ ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ነው።ቀጠናዊ የኃይል አቅርቦት፣የንግድ መስመሮች፣ እንዲሁም የኢንዱስትሪ መዳረሻዎች መፈጠር፣ ለጎረቤት አገራት የኢኮኖሚ እድገት የጋራ ማጠንጠኛ ሆነዋል።   ኢትዮጵያ የምትከተለው የልማት ጎዳና ከድህነት እና ከግጭት ወጥመድ በማውጣት፣ ወደ የጋራ ብልጽግና የሚያመራውን የአፍሪካ ህብረት የ2063 ራዕይ እያሳካ ይገኛል። ኢትዮጵያ በታሪክ አፍሪካ ነጻነቷን እንድታውጅ ከፊት ሆና እንደመራችው ሁሉ፣ ዛሬም በሜጋ ፕሮጀክቶቿ አማካኝነት አፍሪካ ከድህነት ተላቃ የኢኮኖሚ ነጻነቷን እንድታረጋግጥ መሪ ፊታውራሪ ሆናለች። እነዚህ ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆኑ፣የአፍሪካ የኩራት ምንጭና የህልውና መሰረቶች ናቸው።ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለው የልማት እንቅስቃሴ፣ አፍሪካ በራሷ መንገድ የራሷን የልማት ታሪክ እየጻፈች መሆኗን የሚያረጋግጥ ነው። በመሆኑም የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት፣የነገዋ አፍሪካ በዓለም መድረክ ያላት ተጽዕኖ መገለጫ፣ እንዲሁም የጋራ የወደፊት ብልጽግናዋ ዋስትና ናቸው።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በተያዘው የመኸር ወቅት 31 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ ይለማል
Jun 26, 2026 215
አምቦ ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ ዞን በተያዘው የመኸር እርሻ 31 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ የማልማት ስራ መጀመሩን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። የክልል፣ የዞን እና የወረዳ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በዞኑ ኢሉ ገላን ወረዳ የ2018/19 የምርት ዘመን ሩዝን በኩታ ገጠም የማልማት ስራ ተጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ ላይ የተገኙት የምዕራብ ሸዋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ እንደገለጹት፤ በክልሉ መንግሥት በግብርናው ዘርፍ ተቀርጾ ወደ ስራ ከገቡት 33 ኢኒሼቲቮች መካከል የሩዝ ምርት አንዱ ነው።   የሩዝ ምርት በዞኑ በስፋት ያልተለመደ ቢሆንም፣ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ መንግሥት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ህብረተሰቡ በአንድነት በኩታ ገጠም ተደራጅቶ ወደ ስራው መግባቱን ጠቅሰዋል። ዘርፉ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ማሳደግ የሚችል በመሆኑ፣ በ36 ሄክታር መሬት ላይ የሩዝ ዘር መዘራት መጀመሩን ገልጸዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብዲሳ ሀይሉ በበኩላቸው በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል አይነቶች ለመሸፈን ታቅዷል ብለዋል።   ከዚህ ውስጥ ከ31 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነውን መሬት በሩዝ ምርት ለመሸፈን ታቅዶ ስራው ተጀምሯል ብለዋል። የኢሉ ገላን ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርናና መሬት አስተዳደር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ በንቲ በበኩላቸው፣ የወረዳው አርሶ አደሮች የሩዝ ምርት የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴን እየተላመዱ መምጣታቸውን ገልጸዋል።   በወረዳው በ2018/19 የምርት ዘመን 5 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ ምርት ለመሸፈን ታቅዶ፣ የግብርና ግብዓቶችን ለአርሶ አደሮቹ በማቅረብ ዘር የመዝራት ስራ መጀመሩን ጠቁመዋል። ከወረዳው አርሶ አደሮች መካከል ዘውዱ ዘነበ፤ የሩዝ ሰብልን በኩታ ገጠም መዝራት ከጀመሩ አራት ዓመታት እንደሆናቸው ገልጸው፣ ቀደም ሲል ከሄክታር አነስተኛ ምርት ያገኙ እንደነበር አስታውሰዋል።   በአሁኑ ወቅት ግን በግብርና ባለሙያዎች በሚደረግላቸው ሙያዊ ድጋፍ ታግዘው ከአንድ ሄክታር ማሳቸው እስከ 80 ኩንታል የሩዝ ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም