ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ የቡና ምርታማነት የፖሊሲ እርምጃ ለአፍሪካ ሀገራት ጭምር ምሳሌ የሚሆን ተጨባጭ ውጤት አስገኝቷል 
Feb 2, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የቡና ምርታማነት የፖሊሲ እርምጃ ለአፍሪካ ቡና አምራች ሀገራት ጭምር ምሳሌ የሚሆን ተጨባጭ ውጤት ማስገኘቱን የግብርና ሚኒስትር ደኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር) አስታወቁ። ዛሬን ጨምሮ ለሚቀጥሉት ሁለት ቀናት የሚቆየው የአፍሪካ የቡና ሳምንት ከፍተኛ የፖሊሲ ፎረም የአህጉሪቷ ቡና አምራች ሀገራት፣ የልማት አጋሮችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።   የአፍሪካ ቡና ሳምንት ከፍተኛ የፖሊሲ ፎረሙ የቡና ዕሴት ሰንሰለት ተግዳሮቶችን በመለየት የመፍትሔ አቅጣጫዎችን በማመላከት የአየር ንብረት ለውጥ የሚቋቋም የቡና ምርታማነት ሥርዓትን ለማሻሻል ያለመ ነው። በዚሁ ወቅት የግብርና ሚኒስትር ደኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ የቡና ምርታማነትን ለማሻሻል የወሰደቻቸው የፖሊሲ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት አስገኝተዋል ብለዋል። በዚህም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር፣ ለቡና አምራች አርሶ አደሮችና ላኪዎች የሚደረግ ድጋፍና ክትትል የቡና ምርታማነትና የገቢ አቅምን በማሳደግ ለአፍሪካ ቡና አምራች ሀገራት ጭምር ምሳሌ የሚሆን ተጨባጭ ውጤት ማስገኘቱን አስታውቀዋል። የአፍሪካ ቡና አምራች ሀገራትም ዕሴት የታከለበትና ያለቀለት የቡና ምርት ለውጭ ገበያ ማቅረብ የሚያስችል ውጤታማ ትብብርና ተግባራዊ እርምጃን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።   የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት የሚፈጥራቸውን ገበያዎች በመጠቀም የአህጉሪቷን የቡና ምርት ጥራትና የገበያ ተደራሽነትን በማስፋት የጋራ ተጠቃሚነት ዕድሎችን ማጎልበት ያስፈልጋል ብለዋል። በቀጣይም የአፍሪካን የቡና ምርት ተጠቃሚነት ለማሻሻል የዓለም ገበያ የሚፈልገውን ደረጃ ማሟላት የሚያስችሉ የጥናትና ምርምር ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ተወካይ አምባሳደር ሞሀመድ አል አሚን ሱፍ፤ የአፍሪካን የቡና ምርታማነት ለማሻሻል የመንግሥትና የግል አጋርነት ኢንቨስትመንትን ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል።   በዚህም የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን የሚቋቋም የቡና ልማትን ማዕከል በማድረግ አፍሪካ ዕሴት የታከለበት የቡና ምርት ለዓለም ገበያ እንድታቀርብ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በመንግሥታቱ ድርጅት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት ተወካይ ስቴፌን ካርግቦ በበኩላቸው፤ የአፍሪካን የቡና አምራቾችና አቀነባባሪዎች አቅም የሚያሳድግ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።   በቀጣይም የአፍሪካ ሀገራት ቡና አምራች አርሶ አደሮች የሚያጋጥማቸውን ጫና መቋቋም የሚያስችል ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሻፊ ዑመር በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የቡና ልማትና ምርታማነትን ማሻሻል የሚያስችል አቅምና ተሞክሮ ገንብታለች ብለዋል።   በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ተግባራዊ የተደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በቡና ልማት ውጤታማነት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። የአፍሪካ የቡና ሳምንትም ኢትዮጵያ በቡና ምርታማነት ያመጣችውን እመርታዊ ለውጥ ለአህጉሪቷ ቡና አምራች ሀገራት በማስተዋወቅና የገበያ አማራጮችን ለማስፋት ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ አቪዬሽን ደህንነት የማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የአቪዬሽን ዘርፉን ዓለም አቀፍ ተቀባይነት የሚያጠናክር ነው
Feb 2, 2026 46
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አቪዬሽን ደህንነት የማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የአቪዬሽን ዘርፉን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትና ተቀባይነት የሚያጠናክር መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጥር 14/2018 ዓ.ም በ9ኛ መደበኛ ስብሰባው ሶስት የተለያዩ ረቂቅ አዋጆችን ለዝርዝር ዕይታ ለሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴዎች መምራቱ ይታወቃል። በእለቱም የኢትዮጵያ አቪዬሽን ደህንነት አዋጅን ለማሻሻል የቀረበ ረቂቅ አዋጅን ምክር ቤቱ ለዝርዝር ዕይታ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርቷል። በዚህም ቋሚ ኮሚቴው ረቂቅ አዋጁን መርምሮ ሪፖርትና የውሳኔ ሃሳብ ለምክር ቤቱ ለማቅረብ እንዲችል በዛሬው ዕለት የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። በዚህ ወቅት በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የሕግ ዳይሬክተር አማረ ኢቲቻ፤ አቪዬሽን ዘርፍ የድህንነት ስጋት በየጊዜው ተለዋዋጭና ውስብስብ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል።   የአቪዬሽን ደኅንነት ስጋቶች በአስተማማኝ አቅም ለመመከት ለ21 ዓመታት ያገለገለውን የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኩሪቲ አዋጅ ቁጥር 432/1997 ከዓለም አቀፍ አሰራር ጋር በማጣጣም ማሻሻል አስፈልጓል ብለዋል። የቋሚ ኮሚቴው አባላትም የአቪዬሽን ደህንነት አዋጅ ቁጥር 432/1997 ለማሻሻል መነሻ የሆኑ ምክንያቶችንና የባለድርሻ አካላትን የተመለከቱ ጉዳዮች ላይ ምላሽና ማብራሪያዎችን ጠይቀዋል። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ርስቱ ይርዳው፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ተመራጭ ካደረጉት ዋነኛ ጉዳዮች አንዱ የአቪዬሽን አስተማማኝ ደህንነት መሆኑን ገልጸዋል።   በዓለም አቀፍ የሲቪል አቪዬሽን ድርጅት መስፈርት የተዘጋጀው ረቂቅ አዋጅም የኢትዮጵያ አየር መንገድን ተመራጭነት በማስቀጠል የደኅንነት ዘላቂነትን ለማስጠበቅ ጉልህ ድርሻ እንደሚኖረው አስገንዝበዋል። በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የአቪዬሽን ደኅንነት ዳይሬክተር አስራት ቀጄላ፤ ረቂቅ አዋጁ አቪዬሽን ደህንነት የአገልግሎት ክፍያ ደኅንነትን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብለዋል።   የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዲማ ኖጎ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ አቪዬሽን ደኅንነት አስተማማኝነት በዓለም አቀፍ ተቋማት ጭምር ዕውቅናን ያገኘ መሆኑን ተናግረዋል።   ረቂቅ አዋጁም የአቪዬሽን ደኅንነትን የመፈፀም አቅም የበለጠ ማጠናከር እንደሚያስችል ገልጸዋል።   የቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈቲህ መህዲ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ የአቪዬሽን ደኅንነት አስተማማኝነትን በማጠናከር የዘርፉን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትና ተቀባይነት የሚያጠናክር ነው ብለዋል።
በጀትን በአግባቡ ስራ ላይ በማዋል የህዝቡን  የልማት ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ተግባራት ይጠናከራሉ 
Feb 2, 2026 88
ወላይታ ሶዶ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት በጀትን በአግባቡ ስራ ላይ በማዋል የህዝቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገለጸ፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ፕላን ቢሮ የ2018 በጀት አመት የስድስት ወራት የስራ አፈፃፀም ግምገማና በቀጣይ ትኩረት አቅጣጫ ላይ ያተኮረ የሴክተር ምክክር ጉባኤ በወላይታ ሶዶ ከተማ አካሂዷል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ተፈሪ አባተ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ የመንግስት ሃብትን በአግባቡ ስራ ላይ በማዋል የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ነው፡፡ ለዚህም ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁና ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል እንዲኖር ቢሮው ድጋፍና ክትትሉን ማጠናከሩን አንስተዋል፡፡ የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ፍቃደስላስ ቤዛ በበኩላቸው፤ ባለፉት ስድስት ወራት በክልሉ ዘላቂ ልማትን እውን በማድረግ የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ፕሮጀክቶች በእቅድ መመራታቸውን ተናግረዋል፡፡   የክልሉን ሀብት የመለየትና የመንገድ ተደራሽነትን የሚያሳይ ጥናት ተጠናቅቆ ዲጂታላይዝ የማድረግ ስራ መሰራቱንም አመልክተዋል። የመንግስትን ሀብት በአግባቡ ስራ ላይ ለማዋል የባለድርሻ አካላት ቅንጅትን ማጠናከር ላይ ትኩረት መሰጠቱንም አመልክተዋል። የክልሉ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ ቦጋለ ቦሼ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የፕላንና ልማት ቢሮ ከተለመደው አሰራር በመውጣት በውጤት የሚለካ ዕቅድ ላይ በትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።   በዚህም የመንግስትን ሀብት ያማከለና የህዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰው የ2030 ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ግብ ተጥሎ እየተሰራ ስለመሆኑም ተናግረዋል። በምክክር ጉባኤው የክልሉ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በክልሉ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን  ገቢ በአግባቡ በመሰብሰብ ልማት ላይ ለማዋል ትኩረት ተሰጥቷል
Feb 2, 2026 88
ባህር ዳር ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ በመሰብሰብ ልማት ላይ ለማዋል በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ገለፀ። የቢሮው የገቢ ትምህርትና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ታዘባቸው ጣሴ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት፤ በበጀት ዓመቱ ከ100 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል። እቅዱን ለማሳካትም አገልግሎቱን ማዘመንና የአመራርና የባለሙያ ቅንጅትን ማጠናከር ላይ እየተሰራ ነው ብለዋል። አገልግሎቱን ለማዘመን ተግባራዊ የተደረገው የኤሌክትሮኒክስ ታክስ አስተዳደር ስርዓት ግብር ከፋዮች ባሉበት ቦታ ሆነው ግብራቸውን በመክፈል ጊዜንና አላስፈላጊ ወጪያቸውን እንዲቀንሱ ከማስቻል ባለፈ የሚሰበሰበው ገቢ እንዲያድግ እያገዘ መሆኑን አመልክተዋል። ቴክኖሎጂውን በክልሉ ካሉ 257 የታክስ ማዕከላት ውስጥ በ225ቱ ተግባራዊ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል ። በዚህም በሚሰበሰበው ገቢ ልማትን በራስ አቅም ለመሸፈን የሚደረገውን ጥረት እያገዘ መሆኑንም ጠቁመዋል። በክልሉ በበጀት አመቱ እስከ ጥር 22 ቀን 2018 ዓም ድረስ 45 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን ጠቅሰዋል። የተሰበሰበው ገቢ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት በ15 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ጭማሬ እንዳለው አመልክተዋል። የገቢ አሰባሰቡ ማደግም የክልሉን ህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ በተሻለ ደረጃ ለመፍታት እያገዘ መሆኑን አብራርተዋል። በዘርፉ የህግ ተገዥነትን ለማስረፅ ግንዛቤ ከመፍጠር ባሻገር ደረሰኝ ሳይቆርጡ ግብይት ሲፈፅሙ የተገኙ 797 ግብር ከፋይ ነጋዴዎች በገንዘብ መቀጣታቸውንም ተናግረዋል። እንዲሁም በግብር አሰባሰብ ሂደቱ ከአሰራር ውጭ ሲንቀሳቀሱ በተገኙ 133 የገቢ ተቋሙ ሰራተኞች ላይ ከቀላል እስከ ስራ ስንብት የደረሰ የዲሲፕሊን እርምጃ መወሰዱን አመልክተዋል። በቀጣይ ወራትም ዕቅዱን በተሟላ መንገድ ለማሳካት በተሻለ ቅንጅትና ተነሳሽነት እንደሚሰራ አስታውቀዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በኢ-ተገማችና ተለዋዋጭ የዓለም ሁኔታ ውስጥ ተጨባጭ ውጤት አምጥቷል
Feb 2, 2026 60
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በኢ-ተገማችና ተለዋዋጭ የዓለም ሁኔታ ውስጥ ተጨባጭ ውጤት ማምጣቱን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክና ተጠሪ ተቋማትን የ2018 በጀት አመት የስድስት ወር ዕቅድ አፈፃፀም ገምግሟል።   የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) የባንኩንና የተጠሪ ተቋማትን ሪፖርት ለቋሚ ኮሚቴው ባቀረቡበት ወቅት፤ ብሔራዊ ባንክ የኢትዮጵያ የገንዘብና የፋይናንስ ሥርዓት ታማኝ ጠባቂ ነው ብለዋል። በዚህም የዓለም ኢኮኖሚ ባልተረጋጋበት ሁኔታ ውስጥ የዋጋ ግሽበትን አምና ከነበረበት 17 በመቶ አሁን ላይ ወደ 9 ነጥብ 7 በመቶ የነጠላ አሀዝ በማውረድ ስኬታማ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል። የመንግሥት የበጀት ጉድለት ከግምጃ ቤት ሰነድ ሽያጭ እንዲሸፈን መደረጉና የብሔራዊ ባንክ ጥብቅ የገንዘብ አጠቃቀም ፖሊሲ ትግበራ ለዋጋ ግሽበቱ ወደ ነጠላ አሀዝ መውረድ አዎንታዊ ሚና መጫወታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ ልማት ባንክን ጨምሮ ባንኮች 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ገንዘብ በማሰባሰብ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት አንጻር የ33 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት ማስመዝገባቸውን አስረድተዋል። በመደበኛውና በትይዩ ገበያ መካከል ያለውን የምንዛሪ ዋጋ ልዩነት ከፍተኛ ደረጃ መጥበቡን የገለጹት ዶክተር ኢዮብ፥ የባንክ ዘርፍ ተቀማጭ ገንዘብ ክምችት 4 ነጥብ 2 ትሪሊዮን ብር መድረሱን አስገንዝበዋል። ይህም የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በኢ-ተገማችና ተለዋዋጭ የዓለም ሁኔታ ውስጥ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን እንደሚያሳይ አብራርተዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በብዙ አመላካቾች ውጤታማ መሆኑን ጠቅሰው፥ የወጪ ንግድ ገቢን ከ3 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር ወደ 5 ቢሊዮን ዶላር ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ የባንኮችን የተበላሸ የብድር መጠን ከ5 በመቶ እንዳይበልጥ በተከናወኑ ተግባራት በስድስት ወራት ውስጥ የባንኮችን የተበላሸ ብድር ማስተካከል የሚያስችል አበረታች ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል። በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ትርፋማ፣ ጤናማና በቂ የካፒታል አቅም ያላቸው የፋይናንስ ተቋማትን መፍጠር ያስቻሉ ተግባራዊ ውጤቶች መመዝገባቸውንም አንስተዋል።   የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ በበኩላቸው፤ ብሔራዊ ባንክ ጥብቅ የገንዘብ ፖሊሲ በመከተል የዋጋ ግሽበትን ወደ ነጠላ አኃዝ ዝቅ ማድረጉ የሚደነቅ መሆኑን ገልጸዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውም በፋይናንስ ዘርፍ ለዘመናት ሲንከባለሉ የመጡ ችግሮችን መፍትሔ መስጠት ያስቻሉ ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የዲጂታል ፋይናንስ ሥርዓት ለማሻሻል የተከናወኑ አበረታች ተግባራትን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የ2018 ዓ.ም ጥር እና ታህሳስ ወራት ጥቅል ተግባራት
Feb 2, 2026 75
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የ2018 ዓ.ም ታህሳስ እና ጥር ወራት ቁልፍ የሆኑ እና የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም፣ ዘላቂ ሰላም እንዲሁም ሀገራዊ ብልጽግናን እውን ለማድረግ መሰረት የሚጥሉ ተከታታይ ተግባራትን አከናውነዋል። በዚህም በሀገር ውስጥ የብሔራዊ የሎጂስቲክስ ክዋኔ፤ ግዙፍ የአየር ትራንስፖርት መሠረተ ልማት ፕሮጀክት፤ ታዳሽ ኃይል የማስፋት ተግባራት እና አዳዲስ የቱሪዝም መዳረሻ ሐብቶችን በተመለከተ ስኬታማ እንቅስቃሴ አድርገዋል። ሀገራዊ ጉዳዮች እና ስትራቴጂካዊ የልማት ሥራዎች የሀገር ውስጥ ጉዳዮችን በተመለከተ፥ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓልን ምክንያት በማድረግ የዩኒቨርሲቲው የቀድሞ ተማሪ የሆኑት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ “የምሁራን ሚና ለሀገራዊ ብልጽግና” በሚል ርዕስ ጥናታዊ ጽሁፍ አቅርበዋል። እንዲሁም ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የክረምት በጎ አድራጎት መርሃ ግብርን ወደ ላቀ ከፍታ ያሸጋገረውን እና በቤተሰብ ደረጃ ለ150 ዜጎች ምቹና ጽዱ መኖሪያ እንዲሆን ታስቦ የተዘጋጀውን የቱሉ አራራ የተቀናጀ ሞዴል መንደርን በይፋ መርቀዋል። በዚሁ ተመሳሳይ ወር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታን ይፋዊ በሆነ መርሃ ግብር በስፍራው አስጀምረዋል። በመጀመሪያው ምዕራፍ አውሮፕላን ማረፊያው በዓመት 60 ሚሊዮን መንገደኞችን ማስተናገድ የሚችል ሲሆን፤ በታቀደው መሠረት ሙሉ ግንባታው በሚጠናቀቅበት ወቅት በዓመት እስከ 110 ሚሊዮን መንገደኞችን ያስተናግዳል። በወቅቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሀገር የኩራት ምንጭ መሆኑን ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ፤ ይኽ የሆነው ግን ያለተግዳሮት በመጓዙ ሳይሆን በጽናት በተሞላው እንቅፋቶችን የመሻገር አቅሙ እና በአፍሪካ የፋና ወጊነት ሚናው የተነሳ መሆኑን አስምረውበታል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ቁልፍ የመንግሥት ፋይናንስ እና ሌሎች የፋይናንስ ዘርፍ ተቋማትን ባሰባሰበው የኢትዮጵያ “የፋይናንስ እመርታ” ኮንፈረንስ ላይ ተገኝተው ሀገሪቱ እያካሄደች ስላለው የኢኮኖሚ ሪፎርም ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በሌላ በኩል የገና በዓልን ምክንያት በማድረግ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከሚኒስትሮች ምክር ቤት አባላት ጋር በመሆን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ከሚገኙ ሠራተኞች ጋር በዓልን በጋራ አሳልፈዋል። ደህንነት፣ አቪዬሽን እና ብሔራዊ አቅም ግንባታ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የኢፌዲሪ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት ክብረ በዓልን ምክንያት በማድረግ በተሰናዳው የአቪዬሽን ኤክስፖ 2026 ይፋዊ የመክፈቻ መርሃግብር ላይ ተገኝተዋል። እንዲሁም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት አየር ኃይሉ “የጥቁር አንበሳ” የአየር ላይ ትርዒት የተካሄደ ሲሆን፤ ታሪካዊ ሚናውን እና በአሁኑ ጊዜ በተራቀቀ ቴክኖሎጂ የተደገፈውን ከፍተኛ የመፈጸም አቅም በተመለከተ አጽንዖት ሰጥተው ተናግረዋል። ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በታህሳስ ወር መጨረሻ ላይ በአየር ኃይሉ ተገኝተው በስፍራው ምልከታ ያደረጉ ሲሆን፤ ዝግጁነቱን በመገምግም የኢትዮጵያን የመከላከል አቅም አረጋግጠዋል። ቱሪዝም፣ የኃይል መሠረተ ልማት እና ዘላቂ እድገት ጥር ወር በገበታ ለትውልድ መርሃ ግብር አማካኝነት የኢትዮጵያ የቱሪዝም ፖርትፎሊዮ በመሠረታዊነት ጉልህ መስፋፋትን አሳይቷል። የጥብቅ ደን እና የተፈጥሮ ኃብት ስጦታ የሆነው ደንቢ ኢኮ ሎጅ በይፋ መመረቁ፤ በተለይ ኢኮ ሎጅው የሀገሪቱን የቱሪዝም ዘርፍ ባለፉት ሰባት ዓመታት ዘላቂነትን፣ የቅርስ ኃብትን እና ለዘመናት የሚዘልቅ አለም አቀፍ ደረጃን የመጠበቅ እድል መፍጠርን በማዋሃድ ምን ያህል እንደተለወጠ ማሳያ ነው። በተመሳሳይ የሸበሌ ሪዞርት በይፋ የተመረቀ ሲሆን፤ ሪዞርቱ የገበታ ለትውልድ ዋነኛ ፕሮጀክት ሆኖ በ385 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ ነው፡፡ ሪዞርቱ ምግብ ቤቶች፣ ልዩ የባሕል ማዕከል፣ ዘመናዊ የክብረ-በዓላትና የስብሰባ አዳራሾች፣ የሕፃናት መጫወቻ ስፍራዎችና የእግረኛ መንገዶችን የያዘ በመሆኑ፤ እነዚህ የልማት ስኬቶች ኢትዮጵያ በቱሪዝም ዘርፉ በአፍሪካ ቃዳሚ መዳረሻ እንድትሆን ያስችሏታል። በኃይል ልማት ዘርፍ ደግሞ ኢትዮጵያ የአይሻ-2 የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክትን በይፋ በመመረቅ፤ በታዳሽ ኃይል ላይ አዲስ ታሪክ የጻፈ ታላቅ እጥፋት ከመሆኑም በላይ ሀገሪቱ የኃይል አማራጮችን ለማስፋፋት እና አስተማማኝ ለማድረግ የወሰደችው ወሳኝ እርምጃ ምልክት ተደርጎ የሚወሰድ ነው። ይህ አስተማማኝ የኃይል ልማት በቴክኖሎጂ ለተደገፈ ኢኮኖሚያዊ እድገት መሠረት ይጥላል። የገጠር ልማት፣ ትምህርት እና ተቋማዊ ማሻሻያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ጉራፈርዳ ወረዳ ባደረጉት ጉብኝት ሞዴል ገጠር ኮሪደር ስፍራን ተመልክተዋል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከቀዳማዊት እመቤት ጋር በመሆን በሱርማ ወረዳ የተገነባ የትምህርት ቤት ርክክብ ሥነ-ሥርዓት ላይ ታድመዋል። በሌላ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በኢምግሬሽን እና ዜግነት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የተከናወኑ ማሻሻያዎችን በተቋሙ ተገኝተው የተመለከቱ ሲሆን፤ የኢምግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ባለፉት ዓመታት ይስተዋሉበት የነበሩ የአገልግሎት ክፍተቶቹን ለማረም የተለያዩ የለውጥ ተግባራትን ሲያከናውን መቆየቱን ገልጸዋል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኢትዮ- ጂቡቲ ምድር ባቡር አ.ማ ጉብኝት አድርገዋል። በጉብኝቱ እንደ ደረቅ ወደቦች፣ የባቡር መሠረተ ልማት፣ አውራ ጎዳናዎች እና የመጋዘን ግንባታ አስፈላጊ ማሻሻያዎችና ዘመናዊ የማድርግ ሥራዎች በሂደት ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ቀጠናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ተግባራት በዲፕሎማሲያዊው ጎራ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የጂቡቲ እና የሶማሊያ መሪዎችን በጅግጅጋ አየር ማረፊያ ተቀብለው አነጋግረዋል። ይህም ኢትዮጵያ ለክልላዊ ትብብር እና መረጋጋት እያሳየች ያለውን ቁርጠኝነት አጉልቶ ያሳያል። እንዲሁም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ለይፋዊ ጉብኝት ወደ ኢትዮጵያ የመጡትን የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ይን ተቀብለው የወል ፍላጎት በሆኑ የሁለትዮሽ ግንኙነቶች እና ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የዩናይትድ ኪንግደም የኮመንዌልዝ፣ ልማት ጉዳዮች እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይቬት ኩፐርን አግኝተው በቁልፍ የሁለትዮሽ እና ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል። ከውይይታቸው ጎን ለጎን በተካሄደው የኢንቨስትመንት አማካሪዎች ማህቀፍ ሥር የኢንቨስትመንት እና ኃብት አስተዳደር የቴክኒካል ትብብር የመግባቢያ ሥምምነት እና የሁለት የጋራ የልማት ስምምነቶች ፊርማ መርሃ ግብር ላይም ተገኝተዋል። እነዚህም የሁርሶ-አይሻ 400 ኪሎ ቮልት እና የደገሃቡር-ቀብሪደሃር 132 ኪሎ ቮልት የኃይል ማስተላለፊያ ፕሮጀክቶች ስምምነቶች ናቸው። በጥቅሉ በታህሳስ እና ጥር ወር 2018 ዓ.ም የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አመራር ስትራቲጂክ ጠቀሜታ ያላቸውን ፕሮጀክቶች በማፋጠን፤ የታዳሽ ኃይል አቅርቦትን በማስፋፋት፤ የተጠናከረ ብሔራዊ መከላከያ እና የአየር ኃይል እንዲኖር እንዲሁም ንቁ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ የዲፕሎማሲ ተሳትፎ እንዲሳለጥ በማድረግ ረገድ ስኬታማ ተግባራት የተከናወኑበት ነበር። ይህም ኢትዮጵያ ወደ ዘመናዊነት፣ ወደ ጸና ሀገራዊ እድገት እና ዘላቂ ብልጽግናን እውን ለማድረግ የጀመረችውን የስኬት ጉዞ በጠንካራ መሠረት ላይ ያስቀመጠ ተግባር ተደርጎ ይወሰዳል።
በግማሽ ዓመቱ ከ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መሳብ ተችሏል
Feb 2, 2026 68
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦ በ2018 በጀት አመት የመጀመሪያ ስድስት ወራት 2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ዳጋቶ ኩምቤ ገለፁ፡፡ ምክትል ኮሚሽነር ዳጋቶ ኩምቤ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኮሚሽኑ ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር የውጭ ባለሃብቶችን በመሳብ ረገድ አበረታች ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል፡፡ ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ ከ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን አስታውቀዋል፡፡ ይህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ26 በመቶ ብልጫ እንዳለው አመላክተዋል፡፡ በግማሽ ዓመቱ 245 የውጭ ባለሀብቶች አዳዲስ የኢንቨስትመንት ፈቃድ መውሰዳቸውን ገልጸዋል፡፡ እነዚህ ስኬቶች ኢትዮጵያን በአፍሪካ ሁለተኛ በምስራቅ አፍሪካ ደግሞ አንደኛ ቀጥታ የውጭ ኢንቨስትመንት ተቀባይ አገር እንዳደረጓት ተናግረዋል፡፡ የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው እና መንግስት ከግል ባለሃብቶች ጋር የሚያደርጋቸው ተከታታይ ውይይቶች ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ማደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ገልጸዋል፡፡ ፈጣን የመንግስት አገልግሎት እና የመሰረተ ልማት መስፋፋት ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ማደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ሌሎች ዘርፎች መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እና ዲጂታላይዜሽን ፈጣንና ጥራት ያላቸው አገልግሎቶችን ተደራሽ በማድረግ ለውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ማደግ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውንም እንዲሁ፡፡ የንግድ ዘርፉ ለውጭ ኢንቨስተሮች ክፍት መደረጉም ትላልቅ ኩባንያዎችን ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ እያደረገ ነው ያሉት ምክትል ኮሚሽነሩ ባለፉት ስድስት ወራትም 37 የውጭ ባለሀብቶች በዘርፉ ፈቃድ መውሰዳቸውን ጠቅሰዋል።
የመደመር መንግሥት ታላላቅ ፕሮጀክቶችን ጀምሮ ማሳካት  መለያው ነው- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Feb 2, 2026 65
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦የመደመር መንግሥት ታላላቅ ፕሮጀክቶችን ጀምሮ ማሳካት መለያው መሆኑን በ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ አጋማሽ ያከናወናቸው ተግባራት አሳይተዋል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪ የሆኑ አስፈጻሚ ተቋማት የ2018 በጀት ዓመት የግማሽ ዓመት አፈጻጸም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት ተገምግሟል።   ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመክፈቻ ንግግራቸው፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የብልፅግና ዕሳቤ መሬት ነክቶ ፍሬ እያፈራ መሆኑን በማንሳት፥ ለዚህ ደግሞ ተቋማትና የተቋማት መሪዎች ግንባር ቀደም ተዋንያን ናቸው ብለዋል፡፡ የብልፅግና ጉዞ የሚታይና የሚዳሰስ ሥራና ውጤትን የሚፈልግ መሆኑን በመግለጽ፥ በዚህ ረገድ ተጨባጭ ስኬቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰዋል። በ2018 ዓ.ም የአዲስ ዓመት ዋዜማ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ተጠናቅቆ መመረቁን በማውሳት፥ በወቅቱ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ይፋ የሆኑ የጉባ ታላላቅ ብስራቶችም ወደ ትግበራ መግባታቸውን ገልጸዋል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ እንዲሁም የነዳጅ እና የማዳበሪያ ፋብሪካን ጨምሮ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ሜጋ ፕሮጀክቶችን ጀምረናል ነው ያሉት። መንግሥታችን ጀምሮ በፍጥነት መጨረስ መለያው ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪ ተቋማትም አርዓያነት ያለው ሥራ እያከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። የተጠሪ ተቋማት አመራሮች በበኩላቸው፥ በየዘርፋቸው በግማሽ ዓመቱ ያቀዱትን ተግባር በማሳካት በኩል በርካታ ሥራዎችን መተግበራቸውን አንስተዋል።   የፋይናንስ ደህንነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሙሉቀን አማረ፤ የፋይናንስ ስርዓቱና የግብይት ሂደቱ ከወንጀል የጸዳ እንዲሆን እየተሠራ መሆኑን ገልጸው፤ በዚህም ከፍተኛ ለውጥ እየመጣ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ዳጋቶ ኩምቤ፥ በግማሽ ዓመቱ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ26 በመቶ ዕድገት ያለው የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት መሳቡን ጠቅሰዋል።   የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው፣ ኢላማ ተኮር የኢንቨስትመንት ማስተዋወቅ ሥራ፣ ዲጂታል አገልግሎትና አዳዲስ ዘርፎችን ለውጭ ኢንቨስትመንት ክፍት መደረጉ ለተገኘው ውጤት ሚናቸው የላቀ ነው ብለዋል። ሁሉም ተቋማት በሪፎርም ውስጥ መሆናችውን በመግለጽ፤ በሪፎርሞቻቸው የተሟላ አጀንዳ በመያዝ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ጨምሮ በአገልግሎት አሰጣጣቸው በርካታ ውጤቶች ተመዝግበዋል ያሉት ደግሞ የኢሜግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ጎሳ ደምሴ ናቸው።   የመንግሥት አገልግሎትን ማዘመን አማራጭ የሌለው ጉዳይ መሆኑን ያነሱት የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አልማዝ መሠለ በበኩላቸው፥ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢኒሼቲቭ እውን የሆነው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በርካታ ለውጦችን እያመጣ መሆኑን ጠቅሰዋል።   የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለም ፀሐይ ጳውሎስ፥ ባለፉት ስድስት ወራት የተመዘገቡ ስኬቶች አበረታች መሆናቸውን በማንሳት ለቀጣይ የላቀ ውጤት መትጋት ይገባል ብለዋል።   ለዚህም ሁሉም ተቋማት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂን፣ የፋይዳ መታወቂያን፣ የ5 ሚሊዮን ኮደረስ ኢኒሼቲቭን ለማሳካት በተቀናጀ መንገድ መሥራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል። አገልግሎት አሰጣጥን ወደ ዲጂታል ማሸጋገርና ወደ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ማስገባትም ከሁሉም ተቋማት እንደሚጠበቅ ጠቅሰዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በሰጡት ማጠቃለያ፥ የሀገርን የዕድገትና የልማት ጉዞ የሚመጥን ዝግጁነትና ተግባር ከሁሉም ተቋማት እንደሚጠበቅ አፅንኦት ሰጥተዋል።   ኢንቨስትመንትን በመሳብ፣ አገልግሎትን በማቀላጠፍ፣ በገቢ አሰባሰብና በሌሎችም ዘርፎች የተገኙ መልካም ውጤቶች የሚያዘናጉ ሳይሆኑ የላቀ አቅዶ ለመፈጸም መነሻ መሆን አለባቸው ብለዋል። ለዚህም የጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪ ተቋማት እያንዳንዱ የሚያከናውኑት ሥራ ከአንድ ተቋም ያለፈና የኢትዮጵያን ከፍታ የሚገልፅ መሆን አለበት ነው ያሉት። እነዚህ ተቋማት ለሌሎች አካላት ምሳሌ የሚሆን ተግባርና ውጤት እንደሚጠበቅባቸው በማንሳት፥ ኢትዮጵያን በውጤት ለሌሎች ሀገራት ምርጥ ምሳሌ ለማድረግ መረባረብ እንደሚገባ ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ፈጣን የስኬት ጉዞ የአፍሪካ የከተሜነት ውበት መገለጫ እያደረጋት ነው 
Feb 2, 2026 67
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ፈጣን የስኬት ጉዞ የኢትዮጵያ ከተሞች የብልጽግና ተምሳሌት እና የአፍሪካ የከተሜነት ውበት መገለጫ እያደረጋት መሆኑን የመዲናዋ ነዋሪዎች ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በአዲስ አበባ በአጭር ጊዜ የተገነቡ የኮሪደር፣ የወንዝ ዳርና ሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶች ዘመናዊ ከተሜነትን የገለጡ ሆነዋል።   በአዲስ አበባ ተሰናስለው የተገነቡ መሠረተ ልማቶችም ጎስቋላ ገጽታን በዘመናዊ የከተሜነት የአኗኗር ዘይቤ በመቀየር ለነዋሪዎችና ጎብኝዎች ምቹ የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴ ምኅዳርን ፈጥሯል። የአፍሪካ ሕብረት፣ የበርካታ ሀገራት ኤምባሲዎችና ዓለም አቀፍ ተቋማት መቀመጫ እንዲሁም የቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁነቶች የስበት ማዕከል በመሆን ከፍተኛ አድናቆት እየተቸራት ይገኛል። የአዲስ አበባ ከተማ አስደማሚ የዘመናዊ ከተሜነት የልማት ስኬትም የበርካታ ሀገራት መሪዎችና የከተማ ልማት ሙያተኞች በሀገራቸው ለመድገም ከፍተኛ ፍላጎት እያሳዩ መጥተዋል።   የዘንድሮው 39ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ለአባል ሀገራት ተሳታፊዎችም የአዲስ አበባን የልማት ተሞክሮ ለመቅሰም መልካም አጋጣሚ እንደሚፈጥር ይጠበቃል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የመዲናዋ ነዋሪዎች፤ በአዲስ አበባ በየቀኑ የሚታዩ አስደማሚ የልማት ውጤቶች ከኢትዮጵያ አልፎ ለአፍሪካ ከተሞች ጭምር የውበት ተምሳሌት እያደረጋት መሆኑን ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ነዋሪዋ ፍቅር አንለይ፤ ለነዋሪዎችና ጉብኝዎች ምቹ ምኅዳርን የፈጠሩ አስደናቂ የልማት ስኬቶች የኢትዮጵያን የመፈጸም አቅም ምሳሌነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን ገልፃለች።   የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ የአባል ሀገራት ተሳታፊ እንግዶችም የመዲናዋን የዕድገት ጉዞ በማየት የኢትዮጵያን ፈጣን የልማት ግስጋሴ የሚረዱበትን ዕድል ይፈጥራል ብላለች። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ መስፍን ከተማ በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ ፈጣን የለውጥ መንገድ ለነዋሪዎች ምቹ የከተሜነት ዘይቤ በመፍጠር ለሌሎች ከተሞችም በተሞክሮነት የሚያገለግሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።   አዲስ አበባን የሚጎበኙ እንግዶችም በኮሪደርና በወንዝ ዳርቻ ልማት ከተገኙ ስኬቶች ልምድና ተሞክሮ የሚቀስሙበት ዕድል መኖሩን ተናግረዋል። የመዲናዋ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስኬቶች የኢትዮጵያን ትክክለኛ የዕድገት ጉዞና ገጽታ በመግለጥ ለነዋሪዎችና ጉብኝዎቿ ምቹ ምኅዳርን የፈጠሩ ናቸው ያለው ደግሞ እስራኤል አበራ ነው።   የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ተሳታፊዎች በአዲስ አበባ የሚኖራቸው ቆይታም መዲናዋ የአፍሪካዊያን ማዕከል እንደሆነች በተግባር የሚያረጋግጡበት እንደሚሆን ገልጿል። ቅድመ አያቶች የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ የተጎናጸፉትን የነፃነት የድል ታሪክ የአሁኑ ትውልድ በልማት አርበኝነት ለአፍሪካዊያን የሚያስተምርበት ጉዞ ላይ መሆኑን አንስቷል።   በመዲናዋ መናፈሻ ስፍራዎች ያገኘናቸው ዘሚካኤል በላይ በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶች የነዋሪዎችን ማህበራዊ መስተጋብር የሚያጋምዱ ናቸው ብለዋል። የአዲስ አበባ የኮሪደርና ሁለንተናዊ የልማት ለውጦች የህዝብን ተጠቃሚነት ለማሻሻል የሚያስችሉ መሆናቸውን ነው ነዋሪዎቹ የገለጹት ።
በክልሉ ባለፉት ስድስት ወራት የተከናወኑ የልማት ተግባራት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት አሳድገዋል
Feb 2, 2026 62
ወልቂጤ ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የህዝብን ተጠቃሚነት ያሳደጉ ዘርፈ ብዙ የልማት ተግባራት መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። የክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 5ኛ መደበኛ ጉባዔ በወልቂጤ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።   በጉባኤው የስድስት ወራት የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ያቀረቡት ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) እንዳሉት፤ በክልሉ ባለፉት ስድስት ወራት የተከናወኑ የልማት ተግባራት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት አሳድገዋል። የልማት ስራዎቹ የማህበረሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ያረጋገጡና የልማት አቅሞችን ወደ ውጤት ለመቀየር በተደረገው ጥረት የተከናወኑ መሆናቸውን አክለዋል። የግብርናውን ዘርፍ አቅም ለመጠቀም ለአዝርዕትና ሆርቲካልቸር እንዲሁም ለበጋ መስኖ ልማት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱን ጠቅሰው በግብዓት አቅርቦት እና አሲዳማ አፈር በኖራ በማከም ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን አንስተዋል። በዚህም ከ459 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳን በተለያዩ ሰብሎች በማልማት ከ63 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱንም ጠቅሰዋል። በክልሉ ለውጭ ገበያ የሚቀርብ የቅመማ ቅመም ምርት ላይ ትኩረት በመሰጠቱ ከ2 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን አንስተዋል።   ሰው ተኮር ስራዎችን በመተግበር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የአርሶ አደሩን የገቢ አቅም ማሳደግ እንደተቻለም ተናግረዋል። የኑሮ ውድነት ተፅዕኖን ለመቋቋምና ገበያን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ስራዎችን በቅንጅት በመስራት ውጤት መገኘቱን ጠቅሰው ለዚህም በክልሉ 176 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን በማደራጀት አገልግሎት እንዲሰጡ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። በክልሉ ሰባት ከተሞች የአገልግሎት መስጫ የቢሮ ግንባታዎችን ጨምሮ ሌሎች የመንገድ እና የውሃ ፕሮጀክቶች በአጭር ጊዜ ጀምሮ በመጨረስ ውጤታማ ተግባራት እያከናወኑ መሆናቸውን ነው ያረጋገጡት።   በክልሉ አስተናጋጅነት 20ኛው የብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በተሳካ ሁኔታ እንዲከበር ግዙፍ መሰረተ ልማቶችን በወራት ገንብቶ በማጠናቀቅ ውጤታማ መሆን እንደሚቻል አሳይተናል ብለዋል። በመተጋገዝ እና በጋራ ርብርብ ክልሉን ወደ ተሻለ ከፍታ ለማሻገር እየተከናወነ ያለው ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ርዕሰ መስተዳድሩ አመልክተዋል።
የሌማት ትሩፋት ከራስ ፍጆታ ባለፈ ምርቶችን ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን አሳድጓል 
Feb 2, 2026 64
ደሴ ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦ የሌማት ትሩፋት ከራስ ፍጆታ ባለፈ ምርቶችን ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እንዳሳደገላቸው የሐይቅ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ለመቻል በምታደርገው ጥረት ውስጥ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተጀመረው የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ጉልህ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። በተለያዩ አካባቢዎች በግልና በቡድን እየተተገበረ ያለው የሌማት ትሩፋት ከራስ ፍጆታ አልፎ ለገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በብዛትና በጥራት ማምረት አስችሏል።   በመርሃ-ግብሩ የእንስሳት ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ የተሻሻሉ ዝርያዎችን ጨምሮ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ ሁሉም ዜጋ ባለው ቦታ ላይ ምግቡን የሚያመርትበት ብሎም ለገበያ የሚያቀርብበት ዕድል ተፈጥሯል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የሐይቅ ከተማ የሌማት ትሩፋት ተጠቃሚዎችም በመርሃ-ግብሩ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን ነው ያረጋገጡት። አስተያየታቸውን ከሰጡ የከተማዋ ነዋሪዎች መካከል ሻምበል ሀብቴ፣ ከአራት ጓደኞቹ ጋር ተደራጅቶ በተመቻቸላቸው የመሥሪያ ቦታ በዶሮ እርባታ መሰማራቱን ይናገራል።   በወቅቱ በ200ሺ ብር ካፒታል የ45 ቀን ጫጩት በማሳደግ የስጋና እንቁላል ጣይ ዶሮ በማርባት የጀመሩት ሥራ አሁን የዶሮዎቹ ብዛት ከሁለት ሺ መዝለሉንና ካፒታላቸውም ከ2 ሚሊዮን ብር በላይ መድረሱን አመልክቷል። በመርሃ-ግብሩ ከራሳቸው አልፎ ለሌሎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንና ከገቢያቸው ላይ በመቆጠብም ዘመናዊ ሼድ ለመገንባት ቅድመ ዝግጅት ተጠናቋል ብሏል።   በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎችን በመጠቀም የወተት ምርታቸው መጨመሩን የሚናገሩት ደግሞ ሀሊማ አህመድ ናቸው። ከስድስት የወተት ላሞች በቀን ከ50 ሊትር በላይ ወተት በማምረት ለሆቴሎች፣ ለካፌዎችና ለግል ተጠቃሚዎች በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑንም አስታውቀዋል። ከሁለት ጓደኞቹ ጋር በተመቻቸላቸው የባለሙያና የሼድ አቅርቦት በዶሮ እርባታ ተሰማርቶ ውጤታማ መሆኑን የሚናገረው የመርሃ-ግብሩ ተጠቃሚ ሸጋው ካሴ ነው።   አሁን ላይ ከ1ሺ በላይ የ45 ቀን ጫጩቶችን በማሳደግ ለተለያዩ አካባቢዎች በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ መሆኑን ጠቁሞ፣በቀጣይ ሥራውን አስፍቶ ለመስራት ማቀዱን ገልጿል። የደቡብ ወሎ ዞን እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ ተወካይ ስዩም በቀለ፣ በሌማት ትሩፋት ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትንና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በዞኑ ከ148 ሺ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የመስሪያና የመሸጫ ቦታ እንዲሁም የብድር አቅርቦት በማመቻቸት በዘርፉ እንዲሰማሩና ዘላቂ ተጠቃሚነታቸው እንዲረጋገጥ መደረጉንም ገልጸዋል። ባለፉት ስድስት ወራት በሌማት ትሩፋት ወተት፣ ስጋ፣ ማርና የዓሣ ምርት ለገበያ መቅረቡን አብራርተዋል።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት የብልጽግና ዕሳቤ መሬት ነክቶ ፍሬ እያፈራ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Feb 2, 2026 105
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018(ኢዜአ)፦ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የብልጽግና ዕሳቤ መሬት ነክቶ ፍሬ እያፈራ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ባስተላለፉት መልዕክት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ተጠሪ የሆኑ አስፈጻሚ አካላትን የ2018 በጀት ዓመት የግማሽ ዓመት አፈጻጸም ዛሬ ገምግመናል ብለዋል፡፡ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የብልጽግና ዕሳቤ መሬት ነክቶ ፍሬ እያፈራ እንደሆነም ነው የገለጹት።   ለዚህ ደግሞ ተቋማትና የተቋማት መሪዎች ግንባር ቀደም ተዋንያን ናቸው ብለዋል፡፡ የብልፅግና ጉዞ “እየሠራሁ ነው፤ ልሠራ ነበር፤ በመሥራት ላይ ነኝ”፤ የሚሉ ሪፖርቶችን አይቀበልም ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተሠራ መታየት፤ ከተከናወነ መዳሰስ አለበት ነው ያሉት፡፡ በ2018 ዓ.ም የአዲስ ዓመት ዋዜማ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን አጠናቅቀን በጉባ ታላላቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን አብስረናል ብለዋል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት እንዲሁም የነዳጅ እና የማዳበሪያ ፋብሪካን ጨምሮ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ሜጋ ፕሮጀክቶችን ጀምረናል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ መንግሥታችን ጀምሮ በፍጥነት መጨረስ መለያው ነው፤ በዚህ እሳቤ የተጠናቀቁትን ሸበሌ ሪዞርትንና አይሻ-2 የንፋስ ኃይል ማመንጫን አስመርቀናል ብለዋል፡፡ በቅርቡም የምናስመርቃቸው አሉ ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ መንገዶች፣ ድልድዮች፣ ግድቦች፣ ቤቶች፣ እየተገነቡ ናቸው ሲሉም አስታውቀዋል፡፡ የጉባ ብሥራቶች ቀስ በቀስ ሥር ሰድደው ተግባራዊ እየሆኑ ናቸው ሲሉም ጠቁመዋል በመልዕክታቸው፡፡ በዛሬው ግምገማችን የስራ እንቅስቃሴዎቻችንንና ስኬቶቻችንን በልኩ መዝነናል፤ ድክመቶቻችንን ያለ ምሕረት ለማረም ተግባብተናል፤ የመፍትሔ መንገዶችን የሚያመላክትና አዳዲስ ስልቶችን መንደፍ የሚያስችል ገንቢ ምክክር አድርገናል ነው ያሉት። ባለፉት ዓመታት እና በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ ባስመዘገብነው ድል ሳንኩራራ ነገር ግን በልኩ እየተበረታታን በቀጣይ ስድስት ወራት ለላቀ ውጤትና ድል ለመትጋት ተግባብተናል ሲሉም ገልጸዋል፡፡  
በመኸር የለማው በርበሬ አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ ለገበያ መረጋጋት ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል
Feb 2, 2026 56
ጎንደር፤ ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በመኸር የለማው የበርበሬ ምርት አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ ለገበያ መረጋጋት ከፍተኛ ሚና መጫወቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታውቋል። በዞኑ በ2017/18 የምርት ዘመን በ22 ሺህ ሔክታር መሬት ላይ በርበሬ ማልማት መቻሉን በመምሪያው የአትክልትና ፍራፍሬ መስኖ ውኃ አጠቃቀም ቡድን መሪ ሐውልቱ ታደሠ ለኢዜአ ገልጸዋል። የበርበሬ ምርታማነትን ለማሳደግ አዳዲስ ዝርያዎችንና ቴክኖሎጂዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጉንም ጠቁመዋል።   በዞኑ በመኸር እርሻ ከለማው የበርበሬ ሰብልም ከ400 ሺህ ኩንታል የሚልቅ ምርት ለገበያ መቅረቡን አስታውቀዋል። በዚህም መሠረት በምሥራቅና ምዕራብ ደንቢያ እንዲሁም አለፋና ጣቁሳ ወረዳዎች ለገበያ የቀረበው የበርበሬ ምርት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ከማሳደግ ባለፈ ለገበያ መረጋጋት ከፍተኛ ሚና መጫወቱን ነው ያረጋገጡት። ከበርበሬ ምርት ሽያጭ ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገሩት የአለፋ ወረዳ አርሶ አደር ሲሳይ ብዙአየሁ፤ ይህን ሥራም በቀጣይ በማስፋት በይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን እንደሚተጉ ተናግረዋል።   በምዕራብ ደንቢያ ወረዳ የጯሂት ቀበሌ አርሶ አደር ሙላት ጌትነት በበኩላቸው፤ የበርበሬ ምርት በገበያ ተፈላጊና አዋጭ በመሆኑ ከቤት ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጉን አረጋግጠዋል።
የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር ለእንስሳት ዕርባታና ዝርያ ማሻሻል ተግባራት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Feb 2, 2026 58
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፡- የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር ለእንስሳት ዕርባታ እና ዝርያ ማሻሻል ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩ በስፋት እየተሠራበት መሆኑን የሰሜን ሸዋ ዞን እንስሳትና ዓሣ ሀብት መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የእንስሳት ዕርባታ ቡድን መሪ ቤተልሔም አሰፋ ለኢዜአ እንዳሉት፤ መርሐ-ግብሩ ለእንስሳት ዕርባታ የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ ተጠቅሞ አርሶአደሩ ዝርያን የማሻሻል ተግባራት ላይ በትኩረት እየሠራ ነው።   የሌማት ትሩፋቱን ተከትሎ የተፈጠረው ምቹ የእንስሳት ዕርባታና ዝርያ ማሻሻል ሥራ፤ የእንስሳትን ቁጥርና ጥራት በመጨመር፣ የወትት እና የሥጋን ምርታማነት በማሳደግ የአርሶአደሩ ገቢ እንዲሻሻል አስችሏል ነው ያሉት። እንደዞን የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል እንዲሁም ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መምጣቱንም ነው ያረጋገጡት። በዞኑ የባሶና ወራና ወረዳ አርሶ አደር ታደሠ ማሞ እንዳሉት፤ በተሻሻለ ዝርያ ሁለት ላሞችን በማዳቀል በቀን ከአንድ ላም 17 ሊትር ወተት እያገኙ ነው። የወተት ምርቱን ለገበያ በማቅረብም ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ነው የተናገሩት። የሌማት ቱሩፋት መርሐ-ግብሩ ከእንስሳት ቁጥር ይልቅ ጥራት ላይ በማተኮር ምርታማነትን ለማሳደግ እንዳስቻላቸውም ገልጸዋል።   ከዚህ ቀደም ተዳቅለው ከሚታለቡ ሁለት ላሞች ከቤት ፍጆታ ባለፈ በቀን በርካታ ሊትር ወተት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጭ ጌታቸው ማሞ ናቸው ።
የበጋ መስኖ ስንዴን በስፋት በኩታ ገጠም በማልማት ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እየሠሩ መሆናቸውን አርሶአደሮች ተናገሩ
Feb 2, 2026 61
ጭሮ፤ ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፡- ካለፈው ዓመት ልምድ በመውሰድ የበጋ መስኖ ስንዴን በስፋት በኩታ ገጠም በማልማት ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እየሠሩ መሆናቸውን በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የጡሎ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለፁ። አርሶአደሮቹ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ያለፈው ዓመት የኩታ ገጠም እርሻ ምርታማነታቸውን በመጨመሩ በዘንድሮው የበጋ መስኖ ልማት የተሻለ ምርት ለማግኘት መነሳሳት ፈጥሮልናል ብለዋል። በወረዳው የኢፋ አንዶዴ ቀበሌ አርሶ አደር ጌታቸው አበበ እንዳሉት፤ የግብርና ባለሙያዎች ግንዛቤና ድጋፍ በትንሽ ማሳቸው ላይ ብዙ ማምረት አስችሏቸዋል። የመስኖ ልማቱን ለማሳካት የውኃ መሳቢያ ሞተር ከወረዳው ማግኘታቸውንም ገልጸዋል።   ሌላኛው አርሶ አደር ሲራጅ አሊ በበኩላቸው፤ ባለፈው ዓመት ያመረቱት ምርት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸው ዘንድሮ ይበልጥ መነቃቃት እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል። በዚህም መሠረት በዘንድሮው የበጋ መስኖ ልማት ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን ሰብሉን ከአረምና ከበሽታ በመጠበቅ የበለጠ ምርት ለማግኘት እየሠሩ መሆናቸውን ነው የገለጹት።   አርሶ አደሩ በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በመሰማራት ገቢውን እንዲያሳድግ የተደረገው ጥረት ውጤታማ መሆኑን የጡሎ ወረዳ ግብርና እና መሬት ጽሕፈት ቤት የእርሻ ከፍተኛ ባለሙያ የኔሁሉ ዘሪሁን አስታውቀዋል። አርሶ አደሮቹ በትንሽ መሬት ብዙ ምርት በማምረት ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሙያ እገዛ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።   በወረዳው በዘንድሮው ዓመት በበጋ መስኖ ስንዴ ለማልማት ከታቀደው 700 ሔክታር ማሳ ውስጥ አብዛኛው በዘር መሸፈኑን የተናገሩት ደግሞ የጡሎ ወረዳ ምክትል አሥተዳዳሪ ሸምሰዲን ኡስማን ናቸው። አርሶ አደሮቹ ከልማቱ በይበልጥ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምርጥ ዘር እና ፀረ-አረም መድኃኒት እንደቀረበላቸው ተናግረዋል። እንደዞን ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከተዘጋጀው 38 ሺህ ሔክታር በላይ ማሳ እስካሁን 37 ሺህ ሔክታሩ በዘር ተሸፍኖ እየለማ መሆኑን የምዕራብ ሐረርጌ ዞን ግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ጽሕፈት ቤት የስንዴ ልማት አስተባባሪ ሀቢብ አብዱል ከሪም ገልፀዋል።
የኢንዱስትሪ ፓርኩን የኃይል አቅርቦት አስተማማኝ ለማድረግ የሚያስችል ዝርጋታ ተከናወነ
Feb 2, 2026 52
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፡- የአዳማ ኢንዱስትሪ ፓርክን የኃይል አቅርቦት አስተማማኝ ለማድረግ የሚያስችል የኤሌክትሪክ ኃይል መስመር ዝርጋታ መከናወኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስታወቀ። በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ አንዋር አብራር፥ ኢንዱስትሪ ፓርኩ ከዚህ በፊት ከአዋሽ መልካሳ ማከፋፋያ ጣቢያ ኃይል ሲያገኘ መቆየቱን አውስተው፤ የራሱ ብቸኛ መስመር ባለመኖሩ የኃይል መቆራረጥና መዋዠቅ ያጋጥመው ነበር ብለዋል፡፡   አሁን ላይ ከአዳማ ቁጥር 3 የኃይል ማከፋፈያ ጣቢያ በቀጥታ አራት ባለ 33 ኪሎ ቮልት መካከለኛ መስመሮች ለፓርኩ በመዘርጋት አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲኖረው መደረጉን ለኢዜአ ተናግረዋል። የኤሌክትሪክ ኃይል መስመር ዝርጋታው 56 ነጥብ 25 ኪሎ ሜትር መሸፈኑን ጠቁመው፤ በዚህም 800 ባለ 12 ሜትር እና 500 ባለ 14 ሜትር አጠቃላይ 774 የኮንክሪት ምሰሶዎች ተከላ መከናወኑን ገልጸዋል።   ማከፋፈያ ጣቢያው 40 ሜጋ ዋት ኃይል ለፓርኩ በቀጥታ ማቅረብ የሚያስችል ዐቅም እንዳለውም አስረድተዋል። ይህም አምራች ኢንዱስትሪዎቹ አሁን የሚጠቀሙትን የኃይል መጠን በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግና ተጨማሪ አምራቾች ለመሳብ ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ነው ያሉት፡፡   የተዘረጋው የኤሌክትሪክ መስመር የፓርኩን የኃይል አቅርቦት አስተማማኝ ከማድረግ ባሻገር በፓርኩ ተሰማርተው ለሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተጨማሪ ዐቅምን ለመፍጠር፣ ተጨማሪ የሥራ ዕድል ለማስፋፋትና ኢኮኖሚውን ለመደግፍ እንደሚያስችል አስገንዝበዋል። የሀገራችን ኢኮኖሚ እያደገ እና ኢንዱስትሪዎች እየሰፉ መሄዳቸውን ተከትሎ ዘላቂ እና ከፍተኛ ጥራት ያለው የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎት እየጨመረ በመምጣቱ፤ ተቋማችን እነዚህን ፍላጎቶች በፍጥነት፣ በፈጠራ እና በቅልጥፍና ለማሟላት በቁርጠኝነት እየሠራ ነው ሲሉም አስታውቀዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ዓመታዊ ግብርን በየሩብ ዓመቱ መክፈላቸው ጫና እንደቀነሰላቸው ግብር ከፋዮች ገለጹ
Feb 2, 2026 56
ወልዲያ፤ ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፡- ዓመታዊ ግብርን በየሩብ ዓመቱ መክፈል የሚያስችል አሠራር መተግበሩ ግብራቸውን ያለጫና መክፈል እንዳስቻላቸው የሰሜን ወሎ ዞን ግብር ከፋዮች ተናገሩ። በሐራ ከተማ በምግብ ቤት ሥራ የተሰማሩት ሰዒድ መሐመድ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ነጋዴው ባገኘው ትርፍ ልክ ለሀገሩ የሚከፍለው ግብር የሀገሩ ልማት ዋስትና ነው። ዓመታዊ ግብርን በዓመት አንድ ጊዜ መክፈል ጫና እንደነበረው አውስተው፤ አሁን ላይ በየሩብ ዓመቱ መክፈል የሚቻልበት አሠራር መዘርጋቱ እፎይታ እንደሰጣቸው አስረድተዋል።   በሸቀጣሸቀጥ ንግድ የተሰማሩት ማርታ ሁሴን በበኩላቸው፤ ዓመታዊ ግብር በየሩብ ዓመቱ የሚከፈልበት ሁኔታ መዘርጋቱ ለነጋዴው ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንና ግብሩን በወቅቱ ለመክፈል ማስቻሉን ገልጸዋል።   የሰሜን ወሎ ዞን ገቢዎች መምሪያ የግብር ትምህርትና ኮሙኒኬሽን ቡድን መሪ ፍቅር መንግሥቴ፤ ግብር ከፋዩ የተጣለበትን ግዴታ በኃላፊነት እየተወጣ መሆኑን አስታውቀዋል። በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የነበረው የግብር አሰባሰብ በየሩብ ዓመቱ እንዲሆን የተዘረጋው አሠራር ነጋዴው ሳይጨናነቅ ግብሩን እንዲከፍል ማድረጉንም አስረድተዋል። በዞኑ በተያዘነው በጀት ዓመት 3 ቢሊየን ብር ገቢ ለመሰብሰብ መታቀዱንም አመላክተዋል።
የሀገር ውስጥ ገበያውን ለማረጋጋት የሚጥሩ ፋብሪካዎች ሀገራዊ አበርክቷቸው ቀላል አይደለም-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Feb 1, 2026 111
አዲስ አበባ፤ ጥር 24/2018 (ኢዜአ)፦ የሀገር ውስጥ ገበያውን ለማረጋጋት የሚጥሩ ፋብሪካዎች ሀገራዊ አበርክቷቸው ቀላል የሚባል አይደለም ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ አስገነዘቡ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ዛሬ በባሕር ዳር ከተማ የሚገኘውን አማጋ ጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካን መጎብኘታቸውን ገልጸዋል። በቅርቡ ወደ ሥራ የገባው ፋብሪካው፤ ተከላው ሙሉ በሙሉ በቅርቡ ሲጠናቀቅ በዋናነት ብርድ ልብስ፣ የአልጋ ልብስ፣ የሶፋ ልብስ፣ መጋረጃ፣ የአንሶላ ጨርቅ፣ ጂንስ እና ሁሉንም አይነት የጨርቃ ጨርቅ ምርቶች በተለየዩ ዲዛይኖች እና ልኬት ማምረት ያስችለዋል ብለዋል። ጥራት ያላቸው ተኪ ምርቶችን የሚያመርቱና በቀጥታ ምርቶችን ለውጭ ገበያ ከማቅረብ ይልቅ፤ የሀገር ውስጥ ገበያውን ለማረጋጋት የሚጥሩ ፋብሪካዎች ሀገራዊ አበርክቷቸው ቀላል የሚባል አይደለም ሲሉም አስገንዝበዋል።
የግብርና ምርታማነትንና የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተቀየሱ ስትራቴጂዎች እየተተገበሩ ነው
Feb 1, 2026 180
አዳማ፤ ጥር 24/2018 (ኢዜአ)፡- የግብርናን ምርታማነትና የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተቀየሱ ስትራቴጂዎች እየተገበሩ መሆኑን የተለያዩ ክልሎች የግብርና ቢሮ አመራሮች አስታወቁ። የግብርና ሜካናይዜሽን እና የከተማ ግብርና ስትራቴጂዎች፤ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የገቢ ምርቶችን ለመተካት እና የወጪ ንግድን ለማሳደግ የጎላ ሚና እንዳላቸው ይታመናል። በምክትል ርዕሰ መሥተዳድር ማዕረግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ኡስማን ሱሩር እንዳሉት፤ የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታውን ለማሳደግ የግብርና ሜካናይዜሽን እና የከተማ ግብርና ጉልህ ድርሻ አላቸው። ቀደም ሲል ሲሠራ የነበረውን የግብርና ሜካናይዜሽን እና የከተማ ግብርናን በተደራጀ አግባብ ለማስፈጸም የተዘጋጁ ስትራቴጂዎች ተጨማሪ ዐቅም እንደሆኑም አንስተዋል። የከተማ ግብርና ስትራቴጂው ከተሞች ሸማች ብቻ ሳይሆኑ አምራች እንዲሆኑና የሥራ ዕድል እንዲፈጥሩ የሚደረገውን ግብ ለማሳካት አበርክቶው የጎላ መሆኑንም ለኢዜአ ተናግረዋል። የከተማ ግብርና ከኢኮኖሚው ባሻገር የሥነ-ምኅዳር ሚዛንን ለመጠበቅ፣ የሥራ ባህል ለማሻሻል እና የሀብት ምንጭ በመሆንም በርካታ ፋይዳ እያስገኘ መሆኑን አስረድተዋል።   የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ በሪሶ ፈይሳ በበኩላቸው፤ የከተማና የገጠር ግብርና ልማትን ለማሳደግ ሁሉንም አካል ያሳተፈ እንቅስቃሴ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል። በተለይም የዘርፉን የአሠራር ሥርዓት አካታችና አሳታፊ በማድረግ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ የሚወጡ ስትራቴጂዎችን በዕቅድ በማስደገፍ ለተግባራዊነቱ በክልሉ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በክልሉ ሜካናይዜሽንን ለማስፋት በየደረጃው በተደረገው ጥረት አሁን ላይ 50 በመቶ የሚሆነው የእርሻ መሬት በሜካናይዜሽን ታግዞ እየለማ መሆኑንም ለአብነት አንስተዋል። ይህም ምርታማነትን ለማሳደግና የምርት ብክነትን በማስቀረት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ አስችሏል ብለዋል። በቀጣይም ለግብርና ሜካናይዜሽን እና ለከተማ ግብርና ስትራቴጂ ተፈጻሚነት አበክረን በመሥራት የዘርፉን ምርታማነት እናረጋግጣለን ነው ያሉት።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከዩናይትድ ኪንግደም የኮመንዌልዝ፣ ልማት ጉዳዮች እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይቬት ኩፐር ጋር ተወያዩ
Feb 1, 2026 125
አዲስ አበባ፣ ጥር 24/2018 (ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከዩናይትድ ኪንግደም የኮመንዌልዝ፣ ልማት ጉዳዮች እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይቬት ኩፐርን ጋር ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፥ የዩናይትድ ኪንግደም የኮመንዌልዝ፣ ልማት ጉዳዮች እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ይቬት ኩፐርን አግኝቼ በቁልፍ የሁለትዮሽ እና ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይተናል ብለዋል።   ‎ከውይይታቸው ጎን ለጎን በተካሄደው የኢንቨስትመንት አማካሪዎች ማእቀፍ ሥር የኢንቨስትመንት እና ኃብት አስተዳደር የቴክኒካል ትብብር የመግባቢያ ሥምምነት እና የሁለት የጋራ የልማት ስምምነቶች ፊርማ መርሃ ግብር ላይም ተገኝተናል ነው ያሉት። እነዚህም የሁርሶ-አይሻ 400 ኪሎ ቮልት እና የደገሃቡር-ቀብሪደሃር 132 ኪሎ ቮልት የኃይል ማስተላለፊያ ፕሮጀክቶች ስምምነቶች ናቸው ብለዋል።   እነዚህ ስምምነቶች ትብብርን በማጠናከር እና ስትራቴጂያዊ መሠረተ ልማቶችን በማስፋፋት ረገድ ትልቅ ርምጃን የሚያሳዩ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም