ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የብዝሃ ኢኮኖሚ ልማት አቅጣጫን በመከተልና በተደመረ አቅም በማልማት ባለፉት አምስት አመታት የተመዘገበው ስኬት የሚደነቅ ነው
Jul 9, 2026 31
ሐረማያ፤ ሐምሌ 2/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ የብዝሃ ኢኮኖሚ ልማት አቅጣጫን በመከተል አቅምን አካብቶ በተደመረ አቅም በማልማት ባለፉት አምስት አመታት የተመዘገበው ስኬት የሚደነቅ መሆኑን በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የግብርናና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅ ዲንና የአግሪካልቸራል ኢኮኖሚክስ ምሁር የሆኑት ከዲር ጀማል (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 30ኛ መደበኛ ስብሰባ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሁሉም ክልሎች በግብርና፣ ቱሪዝም፣ በመሠረተ-ልማትና በማህበራዊ ዘርፎች በተሰሩ ስራዎች ከፍተኛ ለውጥ እየመጣ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም የወጪ ንግድ ገቢ 11 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን፤ በተለይም ከወርቅ 5 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር እና ከቡና 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱን አብራርተዋል። ኢዜአ የጠቅላይ ሚኒስትሩን ማብራሪያ ተከትሎ ያነጋገራቸው በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የግብርናና አካባቢ ሳይንስ ኮሌጅ ዲንና የአግሪካልቸራል ኢኮኖሚክስ ባለሙያ ከዲር ጀማል (ዶ/ር) ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች የሰጡትን ማብራርያ ስለመከታተላቸው ተናግረዋል። በተለይም ሀገሪቱ ግብርናን በማስፋትና በማዘመን ከሚከናወነው ስራ በተጨማሪ በኢንዱስትሪና በሌሎች የሚከናወኑት ተግባራት አበረታች ውጤቶች ስለመመዝገባቸው ማንሳታቸውን ገልጸዋል። ከለውጡ ማግስት በግብርናው ዘርፍ መሰረቱን በማስፋት የተከናወኑት ተግባራት ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ እድገት፣ በስራ እድል ፈጠራና ድህነትን በመቀነስ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። እንደ ዶክተር ከዲር ገለጻ፤ ቀደም ሲል ሀገሪቱ ካልተጠቀመችባቸው ዘርፎች መካከል ቱሪዝም መሆኑን በመጥቀስ ከለውጡ ወዲህ ትኩረት ተሰጥቶ የተከናወነውና ለውጥ የተመዘገበበት ዘርፉ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን አመልክተዋል። በአሁኑ ወቅት በከተሞች የተገነቡት የኮሪደር ልማት ሰራዎች ቅርሶችን ከማደስና ከመጠበቅ ባሻገር በርካታ ሎጅ ተገንብተዋል፣ ሆቴሎች ተስፋፍተዋል፤ በዚህም የጎብኚው ቁጥር በመጨመር በዘርፉ የሚገኘው ገቢ እያጎለበተ ይገኛል ብለዋል። ከመሰረተ ልማት ጋር በተያያዘም በኮሪደር ልማትና በሌሎች ኢኮኖሚውን አቅምና ፍሰት የሚያጎለብቱና መስተጋብሮችን በቀላሉ የሚያሳልጡ በርካታ ልማቶች መሰራታቸውን ተናግረዋል። በዲጂታል መሰረተ ልማትም የተከናወኑ ተግባራት ኢትዮዽያን ወደ ተሟላ ዲጂታላይዜሽን ያሸጋገሩ ተግባራት ስለመከናወናቸው አንስተዋል። ከለውጡ በፊት 2 ቢሊዮን ዶላር የነበረው ዓመታዊ የውጪ ንግድ ገቢ ባለፉት ዓመታት በተከናወነው ስራ ወደ 11 ቢሊዮን ዶላር ማደጉ መንግስት ምን ያህል የኢኮኖሚ መሰረቱን እንዳሰፋ የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ለቡና ልማት በተሰጠው ትኩረት የተመዘገበው ስኬት በዘርፉ ለተሰማሩ አርሶ አደሮች ትልቅ መነሳሳትን ፈጥሯል
Jul 9, 2026 127
ሮቤ፤ ሐምሌ 2/2018(ኢዜአ)፦መንግስት ለቡና ልማት በሰጠው ትኩረት የተመዘገበው ስኬት የኢክስፖርት ገቢን ከማሳደግ ባለፈ በዘርፉ ለተሰማሩ አርሶ አደሮች ትልቅ መነሳሳትን መፍጠሩን በባሌ ዞን የዘርፉ አመራሮችና ባለሙያዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ተገኝተው፣ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ማብራሪያ ለቡና ልማት የተሰጠው ከፍተኛ ትኩረት ኢትዮጵያን በዓለም ሦስተኛዋ ቡና ላኪ ሀገር እንድትሆን ማስቻሉን ገልጸዋል። አክለውም ሀገራዊ የሪፎርም ሥራው ለውጭ ምንዛሬ ግኝት ስኬቶች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረዋል። በዚህም በዘንድሮው ዓመት ኢትዮጵያ ከሸቀጦች ኤክስፖርት ያገኘችው ገቢ ከ11 ቢሊዮን ዶላር በላይ መሆኑን ገልጸው፣ ከቡና ኤክስፖርት ብቻ በዓመቱ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር መገኘቱን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የኮፊ አራቢካ መገኛ እንደመሆኗ መጠን በየትኛውም ዘመን ቡና ወደ ውጭ ስትልክ መቆየቷን ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ከለውጡ ዓመታት በፊት ግን ይህ ነው የሚባል ገቢ ማግኘት እንዳልተቻለ አስታውሰዋል። በዚህም ሀገሪቱ ባለፉት 17 ዓመታት ቡናን ወደ ውጭ በመላክ በአጠቃላይ ያገኘችው ገቢ 3 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር ብቻ እንደነበር ገልጸው፤ መንግሥት ለቡና ልማት በሰጠው ከፍተኛ ትኩረት ግን በዘንድሮው ዓመት ብቻ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢን ማሳካት መቻሉን አነጻጽረው አብራርተዋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የባሌ ዞን የግብርና ጽሕፈት ቤት አመራሮችና ባለሙያዎች እንዳሉት፤ መንግሥት ለቡና ልማት በሰጠው ትኩረት የተመዘገበው ስኬት በዘርፉ ለተሰማሩ አርሶና አርብቶ አደሮች ትልቅ መነሳሳትን ፈጥሯል።   አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሙአዊያ ፉአድ፤ በዞኑ ባለፉት ዓመታት ለቡና ልማት በተሰጠው ትኩረት ተጨባጭ ለውጥ መመዝገቡን በማሳያነት አንስተዋል። በዞኑ ከለውጥ ዓመታት በፊት በቡና ልማት የተሸፈነው መሬት ከ40 ሺህ ሄክታር እንደማይበልጥ ጠቅሰው፣ ከለውጡ ወዲህ ግን ልማቱን ወደ 78 ሺህ ሄክታር ማሳደግ መቻሉን አመልክተዋል። በተጨማሪም ከአንድ ሄክታር የሚገኘውን የቡና ምርታማነት ከአምስት ኩንታል ወደ 10 ነጥብ 1 ኩንታል ማሳደግ መቻሉም የዘርፉ ትልቅ ስኬት መሆኑን ተናግረዋል። ይህ ውጤት ሊገኝ የቻለው አርሶ አደሩ ያረጁ የቡና ተክሎችን በመጎንደልና ነቅሎ በአዲስ ምርጥ ዝርያ በመተካቱ መሆኑንም ጠቁመዋል።   የቡና ልማትን ለማስፋፋት በተሰጠው ትኩረት በየዓመቱ የሚተከለውን የቡና ችግኝ ከ15 ሚሊዮን ወደ 42 ሚሊዮን ማሳደግ መቻሉን የገለጹት ደግሞ በጽሕፈት ቤቱ የቡና፣ አትክልትና ቅመማ ቅመም ልማት ቡድን መሪ አቶ ወንደሰን ነጋ ናቸው። በዚህም የዞኑ ዓመታዊ የቡና ምርት ከ15 ሺህ ቶን ወደ 44 ሺህ ቶን ማድረስ መቻሉ በዘርፉ ከተመዘገቡ ስኬቶች መካከል ተጠቃሽ መሆኑን አመልክተዋል። በቀጣይም የቡና ልማትን ይበልጥ ለማስፋፋትና በሄክታር የሚገኘውን ምርታማነት ከ21 ኩንታል በላይ ለማድረስ፣ በቴክኖሎጂ የታገዘ ሥራን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ኢኒሼቲቭ ተቀርጾ ወደ ሥራ መገባቱን አክለዋል። አስተያየት ሰጪዎቹ በማጠቃለያቸው፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሰጡት ማብራሪያ ላይ ለቡና ልማት የተሰጠው ትኩረት ኢትዮጵያን በዓለም ሦስተኛዋ ቡና ላኪ ሀገር እንድትሆን ማስቻሉን መግለጻቸው ትልቅ እምርታ መሆኑንና በዘርፉ ለተሰማሩ አርሶ አደሮችም የበለጠ የሥራ መነሳሳትን እንደሚፈጥርም ገልጸዋል።  
የኮሪደር ልማትና ሌሎች ፕሮጀክቶች የዜጎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡና የሀገርን ገጽታ የቀየሩ ናቸው
Jul 8, 2026 405
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):-የኮሪደር ልማትና ሌሎች ፕሮጀክቶች የዜጎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡና የሀገርን ገጽታ የቀየሩ መሆናቸውን የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በትናንትናው ዕለት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 6ኛ የሥራ ዘመን 3ኛ ዓመት 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ከምክር ቤቱ አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው፤ የኮሪደር ልማቱ ዋና ዓላማ የሕዝቡን የኑሮ ደረጃ ማሻሻል፣ ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ ማድረግና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴን ማነቃቃት መሆኑን ጠቅሰዋል። ልማቱ ከከተሞች ደረጃና ውበት፣ ከመሠረተ ልማት ትስስር፣ ከደህንነት እንዲሁም ከመብራት አገልግሎትና ከሌሎች ተያያዥ ጠቀሜታዎች አንጻር ያለውን ፋይዳም አብራርተዋል።   የኮሪደር ልማትና ሌሎች ስትራቴጂያዊ የልማት ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ገጽታ የሚቀይሩ በመሆናቸው፤ መላው ሕዝብ፣ ባለሀብቶችና ተፎካካሪ ፓርቲዎች ለሀገር ግንባታው በጋራ እንዲቆሙ ጥሪ ማቅረባቸውም ይታወቃል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ ባለፉት ዓመታት በኢትዮጵያ በተከናወኑ የኮሪደርና ሌሎች የልማት ሥራዎች የዜጎችን ተጠቃሚነት ከፍ ወዳለ ደረጃ እያሸጋገሩት እንደሚገኙ ገልጸዋል። የልማት ሥራዎቹ ለትውልዱ ትምህርት የሚሰጡና የሥራ ባህልን ለማሳደግ ምሳሌ የሚሆኑ ያሉት ነዋሪዎቹ፥ በአፍሪካም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሀገርን ገጽታ መቀየራቸውን ተናግረዋል። ወይዘሮ ተሊሌ ኃብተማርያም ፤ የኮሪደር ልማትና ሌሎች የልማት ሥራዎች ወጣቶችና ሴቶችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረጋቸውን አንስተዋል።   አቶ ሙደስር ኡመር በበኩላቸው፤ በቅርብ ዓመታት ውስጥ በኢትዮጵያ በተከናወኑ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማቶች ከተሞችን ንጹሕና ለነዋሪዎች ምቹ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። ትውልዱ ከዚህ ትምህርት ሊወስድ፣ በሚከናወኑ ሥራዎች በትጋት ሊሠራና ከመንግሥት ጎን በመሆን ለሀገር ግንባታ አሻራውን ሊያሳርፍ ይገባልም ብለዋል።   ሌላዋ የመዲናዋ ነዋሪ ወይዘሮ አዲስ ዓለም ምስግና በኢትዮጵያ የታየው ለውጥ በአጭር ጊዜ ውስጥ በርካታ ዕቅዶችን ማሳካት እንደሚቻል በተጨባጭ ያመላከተ መሆኑን ተናግረዋል። የልማት ሥራዎቹ በስራ እድል ፈጠራና የኑሮ ደረጃን በማሻሻል የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት አሳድገዋል ያሉት አቶ ታምራት ቶሎሳ፥ ከኢትዮጵያ ባለፈ አፍሪካውያንን ለላቀ ልማት ያነሳሱ ናቸው ብለዋል።      
በክልሉ የገቢ አቅምን በማሳደግ ሁለንተናዊ ልማትን ለማፋጠን የተጀመሩ ሥራዎች ይጠናከራሉ
Jul 8, 2026 217
ወላይታ ሶዶ፤ ሐምሌ 1/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የገቢ አቅምን በማሳደግ የክልሉን ሁለተናዊ ልማት ለማፋጠን የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ አስተዳደር አስታወቀ። በወላይታ ሶዶ ከተማ የ2019 በጀት ዓመት የደረጃ "ለ" ግብር አሰባሰብ እና የንግድ ፈቃድ እድሳት ማስጀመሪያ ንቅናቄ ተካሂዷል።   በንቅናቄ ማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር የኢኮኖሚ ዘርፍ አማካሪ አቶ ሳሙኤል ቀቀቦ እንዳሉት ግብር ለክልሉ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴ ስኬታማነት ጉልህ አስተዋጾ አለው። ክልሉ ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ከእርዳታ ጥገኝነት ከማላቀቅ ባለፈ የክልሉን ልማት በማፋጠን የህዝብን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል ያግዛል ብለዋል። በመሆኑም የክልሉን የገቢ አቅም በማሳደግ የክልሉን ሁለተናዊ ልማት ለማፋጠን የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል። ሁሉም ግብር ከፋይ ግብሩን በአግባቡና ታማኝነት ሲከፍል በገበያው ውስጥ ፍትሃዊና ጤናማ ውድድር ይፈጠራል ያሉት አማካሪው፣ ህገ ወጥ ንግድና የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴን በቅንጅት ለመከላከል ይሰራል ብለዋል።   የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማሪያም በበኩላቸው ከተማ አስተዳደሩ የህዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ እና የከተማዋን እድገት ለማስቀጠል የውስጥ ገቢን አሟጥጦ ለመሰብሰብ ትኩረት መደረጉንም ገልጸዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የግብር ከፋዮን እንግልት ለማስቀረት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዘው የሚሰሩ አምስት የግብር መክፈያ ማዕላትን ወደ ሥራ ለማስገባት መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡   በግብር ዓመቱ በከተማው ካሉ ከ13 ሺህ 790 በላይ የደረጃ "ለ" ግብር ከፋዮች ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ መታቀዱን የተናገሩት ደግሞ የወላይታ ሶዶ ከተማ ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ አማረች ዮሐንስ ናቸው። ሁሉም የግብር መክፈያ ማዕከላት የቴሌ ብር ሲስተምን ጨምሮ የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ከእጅ ንኪኪ ነፃ የሆነ አገልግሎት እንዲሰጡ ሙሉ ዝግጅት ተደርጎ ወደ ትግበራ መገባቱንም ጠቁመዋል። ግብራቸውን በቴክኖሎጂ ታግዘው መክፈላቸው የጊዜና የጉልበት ብክነት እንዳስቀረላቸው የገለጹት ደግሞ አቶ አብርሃም ክፍሌ እና ወይዘሮ ትዝታ ደርጌ የተባሉ የከተማዋ ግብር ከፋዮች ናቸው። ቀድመው መክፈላቸው በኋላ ይገጥማቸው ከነበረ የጊዜ ጥበት እንደሚታደጋቸው ገልጸው፣ ሌሎች ግብር ከፋዮችም ግብራቸውን በታማኝነት ቀድመው በመክፈል ሀገራዊ ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ መክረዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ትናንት በተካሄደ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት እንደሀገር በትሪሊዮን የሚቆጠር ገቢ እንደተገኘ መግለጻቸው ይታወሳል። በግብር ዓመቱ ዲጂታል አሰራር መተግበሩና መደበኛ ካልሆኑ 43ሺህ የንግድ እንቅስቃሴዎች ግብር እንዲሰበሰብ መደረጉ ዘንድሮ የተገኘውን ገቢ ማሳደጉንም አመልክተዋል። ክልሎችም በቀጣይ የገቢ አቅማቸውን በማጠናከር ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ የሚመደብ በጀትን ለታለመለት ዓላማ ማዋል እንዳለባቸው ማስገንዘባቸው የሚታወስ ነው።
በክልሉ በግንባታ ላይ የሚገኙ ፕሮጀክቶችን በፍጥነትና ጥራት እንዲጠናቀቁ የክትትልና ድጋፍ ስራ ይጠናከራል - ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ
Jul 8, 2026 130
ጅግጅጋ፤ ሐምሌ 01/2018(ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል እየተገነቡ የሚገኙ ፕሮጀክቶች በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብ በማጠናቀቅ የክልሉን እድገት ለማፋጠን የክትትልና ድጋፍ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ ገለጹ። በሶማሌ ክልል የተጠናቀቀውን የ2018 በጀት ዓመት የሴክተር ቢሮዎች የአፈጻጸም ግምገማ መድረክ በጅግጅጋ ከተማ መካሄድ ጀምሯል።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ እየተገነቡ የሚገኙ ፕሮጀክቶች በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብ ውስጥ በጥራት ተጠናቀው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገትን ለማፋጠን እንዲያግዙ ተገቢ ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል። የቴክኒክና ሙያ ተቋማት የክልሉ እና የሀገሪቱን ልማት ማፋጠን የሚችል ብቁ የሰው ሀይል እንዲያፈሩ የተጀመሩ የሪፎርም ሥራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። የቴክኒክና ሙያ ተቋማት በራሳቸው አቅም ገቢና ሀብት በመፍጠር፣ የመደበኛና አጫጭር ሥልጠናዎችን የቅበላ አቅም ለማስፋት የጀመሯቸው የሪፎርም ሥራዎችም እንዲሁ መጠናከር እንዳለባቸውም አሳስበዋል። የከተሞች የመሬት አስተዳደር ሥርዓት ወጥ በሆነ አሠራር እንዲመራ በቁርጠኝነት መሥራት እንደሚያስፈልግ ያነሱት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ ይህም የከተሞችን ዕድገት በሚመጥን መልኩ ለመምራት እንዲቻል የመሬት አስተዳደር ሥርዓቱን በዲጂታል አሠራር ማስደገፍና የከተሜነቱን ኑሮ ማሻሻል ላይ ትኩረት ይደረጋል ብለዋል። የከተሞች አደረጃጀት ገቢን የማመንጨት አቅም በማጎልበት በከተሞቹ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ዜጎችን በሥራ እድል ተጠቃሚ የማድረግ ተግባራት ላይ ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው በማስገንዘብ። በመድረኩ ላይ ማብራሪያ የሰጡት የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ አህመድ ሹክሪ፥ በአሁኑ ወቅት በክልሉ እየተገነቡ የሚገኙ የአየር ማረፊያዎች፣ ስታዲየሞች እና የመንገድ ፕሮጀክቶች ግንባታ በጥሩ ፍጥነት ላይ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በቀጣይም እነዚህ የልማት ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት ተጠናቀው ለክልሉ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት የድርሻቸውን ማበርከት እንዲችሉ ተገቢው ክትትልና ድጋፍ እንደሚደረግ ገልጸዋል። በሌላ በኩል የክልሉ ክህሎት እና የሥራ ዕድል ፈጠራ ቢሮ በበኩሉ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ለ174 ሺህ 340 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን በመድረኩ አንስቷል። የቢሮው ኃላፊ አቶ ሀሴን ጋይድ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ወጣቶችን በተለያዩ የሥራ ዘርፎች በማደራጀት ተጠቃሚ የማድረግ ሰፊ ሥራዎች ተከናውነዋል። በዚህም ለ174 ሺህ 340 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልጸው፤ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ተቋማትም ብቁና ተወዳዳሪ የሰው ኃይል አፍርተው ወደ ሥራ ገበያ ማገናኘት እንዲችሉ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ምርት ገበያ በታሪኩ ከፍተኛ የሆነውን የ50 ነጥብ 27 ቢሊየን ብር ግብይት ፈጸመ
Jul 8, 2026 683
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለፈው የበጀት ዓመት የ50 ነጥብ 27 ቢሊየን ብር ግብይት በመፈጸም በታሪኩ ከፍተኛውን ስኬት ማስመዝገቡን ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ መርጊያ ባይሳ አስታወቁ። ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ መርጊያ ባይሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ 214 ሺህ ቶን የግብርና እና የግብርና ያልሆኑ ምርቶች ለገበያ ቀርበው ተገበያይተዋል። በዚህም ተቋሙ በታሪኩ ያስመዘገበው ከፍተኛው የኢኮኖሚ አፈጻጸም ሆኖ ተመዝግቧል። የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ባለፈው የበጀት ዓመት የ50 ነጥብ 27 ቢሊየን ብር ግብይት በመፈጸም በታሪኩ ከፍተኛውን ስኬት ማስመዝገቡን ነው ዋና ስራ አስፈጻሚው የገለጹት፡፡ ቀደም ሲል ተቋሙ በ2011 በጀት ዓመት ያከናወነው የ40 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር ግብይት በከፍተኛ ስኬትነት ይጠቀስ የነበረ ቢሆንም፣ የዘንድሮው የልማት ዕቅድና አፈጻጸም ግን ያንን በላቀ ደረጃ በመብለጥ ስኬታማ መሆኑን አስታውቀዋል። ከግብይቱ በተጨማሪ የምርት ገበያው ያስቀመጣቸውን ግቦች በከፍተኛ ሁኔታ መፈጸም የተቻለበት በጀት ዓመት እንደነበረ ገልጸዋል። ከነዚህም መካከል የመጋዘን ደረሰኝ ብድር በማመቻቸት 1 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር ለአርሶ አደሮች፣ ለህብረት ስራ ዩኒየኖችና ለአቀነባባሪዎች ማስተላለፍ መቻሉን ገልጸዋል። ይህም አርሶ አደሩ ምርቱን አስይዞ ሌላ ተጨማሪ ማስያዣ ሳይፈልግ የአጭር ጊዜ የገንዘብ ፍላጎቱን እንዲያሟላ መደረጉን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የምርት ገበያው ባቋቋመው አካዳሚ አማካኝነት 795 ሰልጣኞችን በቡና ቅምሻ፣ በጥራጥሬና ቅባት እህሎች ጥራት ምርመራ እንዲሁም በአዲስ የኤክስፖርት ማመቻቸት መስክ 46 ሰልጣኞችን ማሰልጠን መቻሉን አብራርተዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ቀደም ሲል ሻጮችና ገዢዎች በአካል በመገኘት ብቻ ያከናወኑት የነበረውን ግብይት ሙሉ በሙሉ ወደ ኦንላይን ማዛወር ተችሏል ሲሉ ገልፀዋል። ይህም ባለድርሻ አካላት ከቤታቸው ወይም ከቢሯቸው ሆነው ያለምንም እንግልት ግብይት እንዲፈጽሙ ማስቻሉን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የምርት ገበያው የግብርና እና የግብርና ያልሆኑ ምርቶችን ጨምሮ ወደ 28 የሚጠጉ የምርት አይነቶችን ለማገበያየት የሚያስችለውን የውል ማዕቀፍ ዝግጅት አጠናቆ ወደ ስራ መግባቱን ጠቁመዋል። በስንዴ ኢኒሼቲቭ አርሶ አደሮችና ማህበራት ምርታቸውን በመጋዘን ደረሰኝ ብድር በማስያዝ ያለ ገንዘብ እጥረት ማገበያየት መጀመራቸውን ገልጸዋል። ይህ አሰራር አምራቾችን በፋይናንስ በመደገፍ የገበያ ትስስሩን ያሳለጠ ታላቅ የልማት ስኬት መሆኑን ዋና ስራ አስፈጻሚው ጠቁመዋል።
በአዲስ አበባ የቤት ኪራይ ጭማሪ ጣሪያ 11.5% ሆኖ ተወሰነ፤ የውል እድሳት ምዝገባም ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል
Jul 8, 2026 324
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ለ2019 በጀት ዓመት የሚተገበረው ፍትሐዊ የቤት ኪራይ ዓመታዊ ጭማሪ ጣሪያ 11.5% ሆኖ መጽደቁን የአስተዳደሩ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ አስታወቀ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዜጎችን የኑሮ ጫና ለመቀነስ እና በኪራይ ገበያው ላይ የሚስተዋሉ ህገ-ወጥና ዘፈቀዳዊ አሰራሮችን በዘላቂነት ለመግታት ታላቅ እርምጃ መውሰዱን ቀጥሏል። ከዚህ ቀደም በወጣው የቤት ኪራይ ቁጥጥር አዋጅ መሠረት፣ ለ2019 በጀት ዓመት የሚተገበረው ፍትሐዊ የቤት ኪራይ ዓመታዊ ጭማሪ ጣሪያ 11.5% ሆኖ መጽደቁን የቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ገልጿል። ይህንን ተከትሎ በመላው ከተማዋ የሚገኙ የግል መኖሪያ ቤቶች የአከራይ-ተከራይ አዲስ የውል እድሳት ምዝገባ ከዛሬ ሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በሁሉም ክፍለ ከተማ ቤቶች አስተዳደር ፅህፈት ቤት በይፋ መተግበር እንደሚጀመርም አስታውቋል። ቢሮው እንዳመለከተው ፣ ይህ የዋጋ ማስተካከያ ውሳኔ በዘፈቀደ የተወሰነ ሳይሆን በከተማዋ ሰፊ ሳይንሳዊ ጥናት ተካሂዶ የነዋሪውን እውነተኛ የመክፈል አቅም ባገናዘበ መልኩ የተዘጋጀ መሆኑን ተመላክቷል። ይህ አሰራር በአንድ በኩል አከራዮች ወቅቱንና የኢኮኖሚ ሁኔታውን ያገናዘበ ፍትሐዊ ገቢ እንዲያገኙ የሚያረጋግጥ ሲሆን፤ በሌላ በኩል ደግሞ ተከራዮች ከገቢያቸው ጋር የተመጣጠነ ኪራይ በመክፈል የተረጋጋ ሕይወት እንዲመሩ ያደርጋል ብሏል። ውሳኔው ያለውን የኑሮ ጫና በከፍተኛ ደረጃ በመቀነስ ረገድ የጎላ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና መልካም አስተዳደር ፋይዳዎች እንዳሉት ቢሮው አረጋግጧል።
የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ትብብርን ለማጠናከር ምቹ ምህዳር ፈጥሯል
Jul 8, 2026 145
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የተገበረችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያና የዲጂታል አገልግሎት መስፋፋት የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ትብብርን ለማጠናከር ምቹ ምህዳር መፍጠራቸውን ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች ገለጹ። በኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በብዝኃ ዘርፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ከተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት መካከል ለንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፉ የተመቻቸ ምህዳር መፍጠር ይገኝበታል። ይህንን ተከተሎም መንግሥት የተለያዩ እርምጃዎችን በመውሰዱ በሀገሪቱ የኢንቨስትመንት ፍሰት እየጨመረ ነው። ኢዜአ ኢትዮጵያ ለውጭ ቀጥታ የኢንቨስትመንት የፈጠረችውን ምቹ ሁኔታ በተመለከተ የተለያዩ ሀገራትን አምባሳደሮችና ተወካዮችን አነጋግሯል። በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር)፥ እስራኤልና ኢትዮጵያ የጠበቀ ኢኮኖሚያዊ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን ገልጸዋል። እስራኤል በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንትና የንግድ ዘርፎች ላይ በመሰማራት ለጋራ እድገት አበክራ እየሰራች እንደምትገኝ ተናግረዋል። እስራኤል ከኢትዮጵያ ቡና፣ ሰሊጥና ሌሎች ምርቶች እንደምታስገባ ጠቅሰው፥ እስራኤልም ያላትን የቴክኖሎጂ አቅምና እውቀት ለኢትዮጵያ በማካፈል ላይ እንደምትገኝ አክለዋል። ኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ተግባራዊ ማድረጓ እና ሀገሪቱ ወደ ዲጂታላይዜሽን የምታደርገው ፈጣን ግስጋሴ፣ በአሁኑ ሰዓት ለኢንቨስትመንት ምቹ ምህዳር ያላት ሀገር እንዳደረጋት ገልጸዋል፡፡ ይህም እስራኤል በኢትዮጵያ ያላትን ኢንቨስትመንት ይበልጥ እንድታስፋፋ ምቹ መደላድል እየፈጠረ መሆኑን ጨምረው አስታውቀዋል፡፡   በኢትዮጵያ የስሪላንካ አምባሳደር ኒርማላ ፓራናቪታና በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በተለያዩ ዓለም አቀፍ እና ቀጣናዊ መድረኮች ለንግድና ለኢንቨስትመንት ዘርፍ ያላትን ምቹ ሁኔታዎች ለማስተዋወቅ የምታደርገውን ጥረት አድንቀዋል፡፡ እንዲሁም የምታቀርባቸው የተለያዩ ማበረታቻዎች ኢንቨስትመንትን በመሳብ ረገድ ትልቅ ሚና እንደሚጫወቱ አስታውቀዋል፡፡ ስሪላንካ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ በጨርቃ ጨርቅ ዘርፍ ላይ በስፋት ኢንቨስት እያደረገች እንደምትገኝ አንስተው፣ በቀጣይም በሌሎች አማራጭ የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ ለመሰማራት ትልቅ ፍላጎትና ቁርጠኝነት እንዳላት ጠቅሰዋል፡፡ በኢትዮጵያ የፓኪስታን የንግድና ኢንቨስትመንት ጉዳዮች ተወካይ ባሲት ሳሊም ሻህ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ለንግድ ግንኙነትና ለኢንቨስትመንት እጅግ ምቹ የሆነ መልክዓ-ምድራዊ አቀማመጥ ያላት ሀገር መሆኗን ጠቅሰዋል።   ፓኪስታን በአሁኑ ወቅት የተወሰኑ የኢትዮጵያ የወጪ ንግድ ምርቶችን ወደ ሀገሯ እያስገባች መሆኑን የገለጹት ተወካዩ፤ ከእነዚህም መካከል ቡና እና ጥራጥሬ ተጠቃሽ መሆናቸውን ገልጸዋል። ፓኪስታን ወደ ሀገሯ ልታስገባቸው የምትፈልጋቸው ዘርፈ-ብዙ ሀብቶች በኢትዮጵያ እንደሚገኙ ጠቁመው፣ በቀጣይም ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የንግድና የኢንቨስትመንት ግንኙነት ይበልጥ ለማሳደግ በትኩረት እየሰራች መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ውብ የቱሪዝም ጸጋዎችን የተቸረች ሀገር መሆኗን ገልጸው፥ ፓኪስታን ኢትዮጵያ ጋር በቱሪዝምና ሌሎች ዘርፎች ትብብርን ለማጠናከር ዝግጁ መሆኗን አረጋግጠዋል።    
ኢትዮጵያ በሀገር ውስጥ ምርት እና የገንዘብ የመግዛት አቅም በምስራቅ አፍሪካ የቀዳሚነቱን ስፍራ ይዛለች - አይኤምኤፍ
Jul 8, 2026 148
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- ኢትዮጵያ በአጠቃላይ በሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) እና በገንዘብ የመግዛት አቅም በምስራቅ አፍሪካ በቀዳሚነት ስፍራ ላይ እንደምትገኝ የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) አስታወቀ። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) በምስራቅ አፍሪካ የሚገኙ 19 ሀገራትን የገንዘብ የመግዛት አቅም (PPP) መሠረት በማድረግ እ.ኤ.አ. በግንቦት 2026 ባወጣው ይፋዊ መረጃ መሠረት፣ የኢትዮጵያ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP በPPP) 558.93 ቢሊዮን ዶላር በመድረስ በምስራቅ አፍሪካ አንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ኢትዮጵያን በመከተል ኬንያ በ435.21 ቢሊየን ዶላር ሁለተኛ፣ ታንዛኒያ ደግሞ በ320.88 ቢሊየን ዶላር ሦስተኛ ደረጃን ይዘዋል። የኢትዮጵያ፣ ኬንያ እና ታንዛኒያ ምጣኔ ሀብት በአንድ ላይ ሲደመር 1.35 ትሪሊየን ዶላር የደረሰ ሲሆን፣ ይህም ቀሪዎቹ 16 የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት በድምሩ ካላቸው አጠቃላይ የኢኮኖሚ መጠን በእጅጉ የሚበልጥ መሆኑ የኢትዮጵያን እና የጎረቤቶቿን የገበያ ግዙፍነት ያሳያል። ከእነዚህ ግንባር ቀደም ሀገራት በመቀጠል ዩጋንዳ፣ ሱዳን፣ ዛምቢያ እና ዚምባብዌ ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ያለውን የምጣኔ ሀብት ደረጃ ይዘዋል። ማዳጋስካር፣ ሩዋንዳ፣ ሞዛምቢክ፣ ማላዊ፣ ሞሪሸስ፣ ሶማሊያ፣ ብሩንዲ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ጅቡቲ፣ ኤርትራ እና ሲሸልስ ደግሞ በቅደም ተከተል ቀጣዮቹ ደረጃዎች ላይ ተቀምጠዋል። በአንጻሩ ኮሞሮስ በ3.43 ቢሊዮን ዶላር የመጨረሻው 19ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።
በደቡብ ወሎ ዞን በግብርናው ዘርፍ የተገኘው አበረታች ውጤት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jul 8, 2026 130
ደሴ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በደቡብ ወሎ ዞን በግብርናው ዘርፍ ቴክኖሎጂንና አዳዲስ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ የተገኘው አበረታች ውጤት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮነን ገለፁ። በዞኑ 15 የእርሻ ትራክተሮች ለአርሶ አደሩ ተከፋፍለዋል።   የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮነን በርክክቡ ወቅት እንደገለጹት፤ በዞኑ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ግብርናውን በማዘመን ምርታማነትን ለማሳደግ የተደረገው ጥረት አበረታች ውጤት ተመዘግቦበታል። ዞኑ በሜካናይዜሽን ለሚካሄድ የሰብል ልማት ምቹ መሆኑን ጠቁመው፣ እየተመዘገበ ያለውን ውጤት ለማስቀጠልም 15 የእርሻ ትራክተሮችን ለወረዳዎች ማስረከብ መቻሉን አስረድተዋል። በዚህም በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ጥራትና ብዛት ያለው ምርት በማምረት ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው፣ በዞኑ ግብርናውን ከኋላ ቀር አሰራር በማውጣት ወደ ዘመናዊ የአስተራረስ በዘዴ በመከተል ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው።   በዚህም አርሶ አደሩ የምግብ ዋስትናውን ከማረጋገጥ ባለፈ ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለገበያ የሚተርፍ ምርት ማምረት የሚያስችል አቅም መፍጠሩን ተናግረዋል። ይህም የምርት ማሳደጊያ ቴክኖሎጂዎችንና አዳዲስ አሰራሮችን በተገቢው ሁኔታ በመተግበር የመጣ ውጤት መሆኑን አስረድተዋል። የመጣውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠልም ዛሬ የተሰራጩትን ጨምሮ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 37 የእርሻ ትራክተሮችን በማሰራጨት በአጠቃላይ በዞኑ ያሉ የትራክተሮች ቁጥርን 89 መድረሱን አረጋግጠዋል። "በዘመናዊና የተሻሻለ የግብርና አሰራር ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ተችሏል" ያሉት ደግሞ የለጋምቦ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሁሴን ሙላት ናቸው።   አርሶ አደሩ ሜካናይዜሽን አሰራርን እየተላመደ በመምጣቱ የቴክኖሎጂ ጥያቄው መስፋቱን ጠቁመው፣ ዛሬ የተረከቧቸውን ሁለቱን ጨምሮ 15 ትራክተሮች በስራ ላይ እንደሚገኙ አስገንዝበዋል። በርክክቡ ወቅት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር)፤የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ እና ሌሎች አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ ለዘላቂ ሰላምና የልማት ስራዎች ስኬት የመንግስትን ቀጣይነት ያለው ቁርጠኝነት ያረጋገጠ ነው
Jul 8, 2026 103
ሰመራ፤ ሐምሌ 1/2018(ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በትላንትናው ዕለት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰጡት ማብራሪያ ለዘላቂ ሰላምና የልማት ስራዎች ስኬት የመንግስትን ቀጣይነት ያለው ትጋትና ቁርጠኝነት ያረጋገጠ መሆኑን በአፋር ክልል የሰመራ ሎጊያ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በትናንትናው ዕለት ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ መስጠታቸው ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸውም መንግስት በተለይም ለዘላቂ ሰላም፣ ለንግግርና ውይይት ሁልጊዜም ዝግጁ መሆኑን አስረድተዋል። የግጭትና ጦርነት እሳቤ አውዳሚና ትርፍ የሌለው መሆኑን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚያስፈልገን ሰላም፣ ትብብር እና አብሮነት ነው ብለዋል። ከዚሁ ጋር በተገናኘ በአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያ ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ ለዘላቂ ሰላምና የልማት ስራዎች ስኬት የመንግስትን ቀጣይነት ያለው ትጋትና ቁርጠኝነት ያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል አቶ ዋሲሁን አያሌው፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምክር ቤት ተገኝተው የሰጡት ማብራሪያ ዘርፈ ብዙ ጉዳዮችን የዳሰሰ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የሰላም ጉዳይ ወሳኝ መሆኑን በማንሳት የግጭትና ጦርነት እሳቤ አውዳሚና ትርፍ የሌለው በመሆኑ የሰላም ጥረታችን ተጠናክሮ ይቀጥላል ማለታቸው መንግስት ለሰላም ያለውን ጽኑ አቋም ያረጋገጠ ነው ብለዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ የትኛውንም ችግር በውይይትና በንግግር መፍታት አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት የሰጠ በመሆኑ ሁላችንም የሰላምን ጉዳይ የራሳችን አጀንዳ አድርገን መስራት አለብን ነው ያሉት። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ ወጣት ሙሳ መሐመድ በበኩሉ፥ ባለፉት አምስት ዓመታት ሁላችንንም ተጠቃሚ ያደረጉ በርካታ የልማት ሥራዎች ተሰርተዋል ይህንንም በበቂ ማሳያዎች መግለጽ ይቻላል ብሏል። በመሆኑም በልማት የተገኘውን ስኬት በሰላም ግንባታም በመድገም ለሁለንተናዊ እድገትና የጋራ ተጠቃሚነት መስራት ይገባናል ሲል ገልጿል። አገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታላይዝ በማድረግ፣ በከተሞች አካባቢ ቀልጣፋ የአገልግሎት ተጠቃሚነትን በፍጥነት ማሳደግ መቻሉን የገለጹት ደግሞ አቶ ረምዚ ይማም ናቸው። የትምህርት ጥራትን በማረጋገጥ ረገድም አሁን ባለው ሁኔታ እየተከናወኑ ያሉት ሥራዎች አበረታች መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በትምህርት ዘርፉ በርካታ ሞዴል ትምህርት ቤቶች መገንባታቸን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚገባ መግለጻቸውን ተናግረዋል።
በምዕራብ ወለጋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ470 በላይ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቅተዋል
Jul 8, 2026 108
ጊምቢ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የሕዝቡን የልማት ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ከ470 በላይ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት መብቃታቸውን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ተሊላ ተረፋ ገለጹ። ዋና አስተዳዳሪው እንደተናገሩት፤ ለአገልግሎት የበቁት እነዚህ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች የተገነቡት ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ነው። በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ተጠናቀው ወደ ሥራ ከገቡት የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች መካከል የንጹሕ መጠጥ ውኃ ተቋማት፣ የአነስተኛና ጥቃቅን ማኑፋክቸሪንግ ሼዶች፣ የመስኖ ልማት መሠረተ ልማቶች፣ የገጠርና የከተማ መንገዶች እንዲሁም የጤና ኬላዎች እና የትምህርት ተቋማት ናቸው ብለዋል።   የእነዚህ ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ መግባት በአካባቢው የሰፈነውን ሰላም ከማጽናት ባለፈ፣ ሕዝቡ ልማቱን በማፋጠን የራሱን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ እንቅስቃሴዎች በንቃት እንዲያሳልጥ ትልቅ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። የዞኑ ነዋሪዎች በበኩላቸው ፤ በአካባቢው የተገነቡት ፕሮጀክቶች የሕዝቡን የቆየ የመልማት ፍላጎት በትክክል የመለሱ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዞኑ የተገነቡት የትምህርትና ጤና ተቋማት በቅርበት አገልግሎት እንድናገኝ እያስቻሉን ነው፤ ይህም ገንዘብና ጉልበታችንን በመቆጠብ በሌሎች የልማት ሥራዎች ላይ እንድንተጋ አግዞናል ብለዋል።   እንዲሁም በአካባቢያችን የተገነቡ የመንገድ መሰረተ ልማቶች ምርታችንን በቀላሉ ወደ ገበያ በማድረስ ተጠቃሚ እንድንሆን እያገዘን ነው ሲሉም ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም የአካባቢያችንን ሰላምና ልማት ዘላቂ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከምንጊዜውም በላይ የበኩላችንን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ ነን ብለዋል።
በሐረሪ ክልል በኮሪደር ልማቱ የተከናወኑት የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች ጎብኚዎችን እየሳቡ ነው
Jul 8, 2026 84
ሐረር፤ ሐምሌ 1/2018(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በኮሪደር ልማቱ የተከናወኑት የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ተግባራት የቱሪስቶችን ፍሰት በከፍተኛ ሁኔታ እያሳደጉ መሆኑን በክልሉ በአስጎብኚነት የተሰማሩ ባለሙያዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል ሰሞኑን በሰጡት ማብራሪያ በዘርፉ የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን አንስተዋል። የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በማሳያነት አቅርበዋል። በሐረር የሚገኙ ጥንታዊ፣ ሃይማኖታዊና ታሪካዊ ቅርሶች እድሳትና የኮሪደር ልማትና ስራዎች ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ትልቅ አቅም ከመሆናቸው ባለፈ ጎብኚዎችን እየሳቡ መሆኑ ተገልጿል። የዘመናት ዕድሜ ያላቸው እነዚህ ቅርሶችን ከተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ አደጋዎች ለመታደግ በክልሉ መንግሥትና ባለድርሻ አካላት አማካኝነት የተቀናጀ የኮሪደር ልማት፣ የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራ ሲከናወን ቆይቷል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የጀጎልን ታሪካዊ ይዘት ሳይለቁ የተከናወኑ የጥገናና የማደስ ሥራዎች፣ የቱሪስት መናኸሪያዎችን የማስዋብ እንዲሁም የከተማዋን የምሽት ገጽታ የሚቀይሩ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች የቅርሶቹን ዕድሜ ከማራዘም ባለፈ ለጎብኚዎች ምቹና ሳቢ አካባቢን መፍጠር ችለዋል። ይህ አቀራረብ በተለይ የውጭና የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች በከተማዋ የሚኖራቸውን ቆይታ እንዲያራዝሙና በባህላዊ እሴቶች ላይ ያላቸውን ልምድ እንዲያበለጽጉ ትልቅ ዕድል ፈጥሯል። የቅርስ ጥበቃና ማሻሻያ ሥራዎቹ የክልሉን የቱሪዝም ገቢ ከማሳደግ ባለፈ፣ በቀጥታ በአስጎብኚነት፣ በሆቴል አገልግሎትና በባህላዊ እደ-ጥበብ ምርቶች ሽያጭ ላይ ለተሰማሩ የአካባቢው ማህበረሰብ አባላት ሰፊ የሥራ ዕድልና የገቢ ምንጭ በመሆን የላቀ ፋይዳ እያበረከተ ይገኛል። በክልሉ በአስጎብኚ ስራ የተሰማራው ሐይሉ ጋሻው እንደሚገልጸው፤ የጀጎል ዓለምአቀፍ ቅርስን ጨምሮ በከተማና ገጠር ወረዳ የሚገኙ ታሪካዊና ጥንታዊ ቅርሶች የጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች ተሰርተዋል። እነዚህ የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች እንዲሁም ሸዋል ኢድን ጨምሮ የሚከናወኑ ክብረ በዓላት የሀገር ውስጥም ሆነ የውጪ ጎብኚዎችን በመሳብ በኩል አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም የቱሪዝም ዘርፉን ለማጎልበት የክልሉ መንግስት በተለያዩ አማራጮች ያከናወነው የማስተዋወቅ ስራ ባለሀብቶች በከተማው ሪዞርቶችና ሆቴሎች እንዲገነቡ እድል መፍጠሩንም ተናግሯል። እንዲሁም በዘርፉ ለተሰማሩ ባለሙያዎች እየተሰጡ የሚገኙ ስልጠናዎችም ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ጠቁመዋል። ሌላው አስጎብኚ ቴዎድሮስ በላይ በበኩሉ፤ በከተማው በኮሪደር ልማት የተከናወኑት ስራዎች በቱሪዝም ዘርፉ ላይ መነቃቃትን መፍጠሩንና ከተማዋን ውብና ጽዱ ከማድረግ ባለፈ ጎብኚው ተመልሶ እንዲመጣ እያስቻሉ መሆኑን ገልጸዋል። በኮሪደር ልማት የተከናወኑት ስራዎች ቅርሶች ተጠብቀው እንዲቆዩና ለትውልድ እንዲተላለፉ ያስቻሉ መሆኑ አመልክተዋል። በክልሉ ጎብኚው የሚያርፍባቸው ሆቴሎችና ሪዞርቶችን ከማስፋፋት አንጻር እየተከናወኑ የሚገኙ አበረታች ስራዎችም ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠቁመዋል። የሐረሪ ክልል የቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሚ አብዱልዋሲ፤ በክልሉ በቱሪዘም ዘርፍ በተሰጠው ትኩረት የቱሪዝም መስህቦችን በማልማት፣ የጎብኚዎችን ቆይታ በማራዘምና ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ አቅም በማሳደግ በኩል የተሻሉ ተግባራት መከናወናቸውን መግለጻቸው ይታወሳል።
በኢትዮጵያ እየተገነቡ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በማነቃቃትና በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያሳዩ ነው
Jul 8, 2026 173
አሶሳ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ እየተገነቡ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በማነቃቃትና በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያሳዩ መሆኑን በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህር የሆኑት ሙሐመድ ኢብራሂም ገለጹ። ኢትዮጵያ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት የሀገሪቱን የረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማረጋገጥና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያስችሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ እየሰራች ትገኛለች። ከእነዚህም መካከል በታዳሽ ኃይል ማመንጫ፣ በታላላቅ የትራንስፖርት መሠረተ ልማቶች፣ በኢንዱስትሪ ፓርኮች እንዲሁም በከተማ ውበትና በኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች ሰፊ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ እየተገነቡ ይገኛሉ። እነዚህ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች በሚገነቡበት ወቅት በርካታ የሥራ ዕድሎችን በመፍጠር፣ የሀገር ውስጥ ምርታማነትን በማሳደግና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ረገድ የጎላ ሚና እንዳላቸው የዘርፉ ባለሙያዎች በተደጋጋሚ ይገልጻሉ። ትናንት በተካሄደው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ጀምራ በማጠናቀቅ ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት እያስመዘገበች መሆኑን ተናግረዋል። መንግሥት በአሁኑ ወቅት የጀመራቸውን ሜጋ ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት በማጠናቀቅ ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ባለበት በዚህ ወቅት፣ የፕሮጀክቶቹ ተጨባጭ የኢኮኖሚ ፋይዳ በምሁራንና በባለሙያዎች ዘንድ ሰፊ ትኩረት እየተሰጠው ይገኛል። ፕሮጀክቶቹ የሕዝቡን የዕለት ተዕለት ኑሮ የሚያሻሽሉ እና የኢትዮጵያን ጀምሮ የመጨረስ አቅም በይፋ የሚያረጋግጡ እንደሆኑ አንስተዋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህር የሆኑት ሙሐመድ ኢብራሂም እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በብዝሃ ዘርፍ ላይ ያተኮረ መሆኑ በሁሉም ዘርፎች ተመጣጣኝ የሆነ የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲመዘገብ አግዟል። በተለይም ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የሚያመነጩት ገቢ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያሳዩ እንደሆነ ጠቁመው፤ ይህም የሀገሪቷን ገቢ እና ወጪን በማስተካከል ጤናማ የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲመዘገብ አድርጓል ብለዋል። ይህም የሀገሪቷ ዓመታዊ በጀት በየጊዜው ጭማሪ እንዲያሳይ እንዲሁም ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም እንዲያድግ አይነተኛ ሚና እንዳለው አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በማዕድን፣ በኢንዱስትሪ እና በአግሮ ኢንዱስትሪ ዘርፎች ያከናወነቻቸው የሪፎርም ተግባራት ሀገሪቱን በምስራቅ አፍሪካ ቀዳሚ የኢኮኖሚ ባለቤት እንደሚያደርጋትም ትልቅ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ "ብሪክስን" ጨምሮ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር የጀመረችው የንግድ ግንኙነት እና የወጪ ንግድ መጨመር የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ተወዳዳሪነት የሚያሳድግ እንደሆነም አንስተዋል።
ኢትዮጵያ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመተካት የሄደችበት መንገድ ተጨባጭ ለውጥ እያሳየ ነው - ምሁራን
Jul 8, 2026 173
ጅማ ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- ኢትዮጵያ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የሚያስወጡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት ለመተካት የሄደችበት መንገድ ተጨባጭ ለውጥ እያሳየ መሆኑን ምሁራን ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ትላንት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሰጡት ማብራሪያ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማስፋፋትና ለማዘመን ከተያዙ ቁልፍ ዘርፎች መካከል የኢንዱስትሪው ክፍለ-ኢኮኖሚ ዋነኛውና የትኩረት ማዕከል መሆኑን ጠቅሰዋል። ከለውጡ በፊት በሀገሪቱ የነበሩ ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ከ47 በመቶ በታች እንደነበር ጠቅሰው፤ ለዚህም እንደ ፋይናንስ፣ መሬትና የኃይል አቅርቦት ችግሮች በምክንያትነት ይጠቀሱ እንደነበር ገልጸዋል። ይህንን ችግር ለመቅረፍ መንግሥት ልዩ ኮሚቴ በማቋቋም እያንዳንዱን ኢንዱስትሪ በመጎብኘትና ችግሮቻቸውን በየደረጃው ለመፍታት ባደረገው የተቀናጀ ጥረት፣ ቀድሞ የነበሩ ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅማቸው ዛሬ ላይ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማለቱን ተናግረዋል፡፡ እያደጉ የመጡት የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪዎች በርካታ ምርቶችን በሰፊው በማምረት ከውጭ የሚገቡትን ምርቶች በሀገር ውስጥ ከመተካት ባለፈ፣ ወደ ውጭ የሚላከውን መጠን ከፍ አድርገውታል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የዘርፉ ምሁራን እንደገለጹት፤ መንግስት ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመተካት የሄደበት መንገድ ተጨባጭ ለውጥ እያሳየ ነው። በድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የቢዝነስ እና ኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል መምህር መስፍን መኮንን (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ ባለፉት ዓመታት የውጭ ምንዛሬ እጥረት በትልቅ ተግዳሮትነት የቆየ ቢሆንም አሁን ላይ ግን ችግሩ በፍጥነት እየተቀረፈ ይገኛል። አዳዲስ የኢንዱስትሪ ፓርኮች መገንባታቸውና የማምረት አቅማቸው በየጊዜው እንዲያድግ በተደረገው ጥረት በኢትዮጵያ ታሪክ ከፍተኛ የሆነ የውጭ ምንዛሬ ማዳን ተችሏል ብለዋል። አክለውም ኢንዱስትሪዎች የሀገር ውስጥ ምርቶችን በቀላሉና በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ በማቅረብ የውጭ ምርቶችን እያስቀሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ለዚህም የጨርቃ ጨርቅና የቆዳ ውጤቶችን ለአብነት በማንሳት በዚህ ሂደት እያደገ የመጣውን የሀገሪቱን የዲጂታል የቴክኖሎጂ አቅም አጋዠ እንደነበርም ገልጸዋል። በተጨማሪም በምግብ ራስን ለመቻል ግብርናውን አዘምኖ በስፋት የማምረት ስራ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ መሆን የሚችል መሆኑን በመግለጽ፣ መንግስት በቀጣይ ይፋ ያደረጋቸውና እየሰራባቸው ያሉ ጉዳዮች ከዚህ የተሻለ ለውጥ እንደሚያመጡ ተናግረዋል። ከውጭ የሚገቡ መድኃኒቶችን አስቀርቶ በሀገር ውስጥ የማምረት አቅም እያደገ መምጣቱ፣ እንዲሁም የማዳበሪያ ፋብሪካ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በመገንባት ከውጭ የሚገቡ የግብርና ግብዓቶችን ለማስቀረት የታቀደው ስራ ሀገሪቱን ወደፊት ተወዳዳሪ የሚያደርግ መሆንንም አስረድተዋል። በጅማ ዩኒቨርሲቲ የግብርና ምጣኔ ባለሙያ እና ተመራማሪ አደባ ገመቹ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ እንደ ስንዴ እና ሩዝ ያሉ ሰብሎችን በስፋት በማምረት ከውጭ የሚገባውን ምርት ለመቀነስና ለማስቀረት ስኬታማ ስራዎችን ማከናወኗን ገልጸዋል። ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመሸፈን የሚደረገው ጥረት ለወጣቶችና ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የስራ እድል እና የገበያ ትስስር እየፈጠረ ይገኛል ብለዋል። ቀደም ሲል በሀገር ውስጥ አይመረቱም ተብለው ይታሰቡ የነበሩ ምርቶች አሁን ላይ በጥራት እየተመረቱ መሆኑን በመጥቀስ ይህም የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎችንና ምርቶችን ማበረታታት በአቅርቦት ሰንሰለቱ ውስጥ ተጨማሪ የስራ እድሎችን ይፈጥራል ብለዋል። ይህ ጥረት በምግብ ምርት ላይ ያለንን የውጭ ሀገራት ጥገኝነት በመቀነስ፣ ሀገራዊ የምግብ ዋስትናን በአስተማማኝ ሁኔታ ለማረጋገጥ የሚረዳ በመሆኑ ኢትዮጵያ ለዚህ ተጨባጭ ስኬት በትጋት እየሰራች መሆኗን ገልጸዋል፡፡ የፋብሪካዎች መስፋፋትም ለዚህ ግብ መሳካት መሠረት እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቁመዋል።
በባሌ ዞን በበጀት ዓመቱ ከ700 በላይ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት ተሸጋግረዋል
Jul 8, 2026 191
ሮቤ ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን በበጀት ዓመቱ 719 ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን የዞኑ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በተሰማሩበት የሥራ መስክ ውጤታማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩ አርሶ አደሮችና ማኅበራት የተደረገላቸው ማበረታቻ ለተሻለ ሥራ እንደሚያነሳሳቸው ገልጸዋል። የዞኑ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መሐመድ ኢብሮ እንዳሉት፤ በዞኑ አርሶ አደሩ በተሰማራበት የሥራ መስክ ውጤታማ በመሆን መዋቅራዊ ሽግግር እንዲያደርግ ድጋፍ እየተደረገ ነው። በዚህም በዞኑ እየተገባደደ በሚገኘው የበጀት ዓመት 719 የሚሆኑ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት በመሸጋገር የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው ሥራ ውስጥ መግባታቸውን አመልክተዋል። አርሶ አደሮቹና ኢንተርፕራይዞቹ ባለፉት ዓመታት በተሰማሩበት የሥራ መስክ ውጤታማ ከመሆን ባሻገር በነፍስ ወከፍ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገባቸውን ተናግረዋል። አርሶ አደሮቹና ማኅበራቱ ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩት ባስመዘገቡት 2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ካፒታል መሆኑንም አስረድተዋል። የተሸጋገሩት አርሶ አደሮች ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገቡ ከ14 ሺሕ 400 ለሚበልጡ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥሩም አክለዋል። ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች ከተሰማሩባቸው የሥራ መስኮች መካከል ማኑፋክቸሪንግ፣ አገልግሎት፣ ኢንዱስትሪና ሌሎችም ዘርፎች ይገኙበታል ብለዋል። ለተሸጋገሩ አርሶ አደሮች በተሰማሩበት የሥራ መስክ ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆኑ የመሬት አቅርቦትን ጨምሮ ሌሎች የብድርና የተለያዩ ማበረታቻዎች እንደሚደረግላቸውም ተናግረዋል። አቶ መሐመድ እንዳሉት፤ በዞኑ ባለፉት ዓመታት በግብርናው ዘርፍ የተከናወነው ውጤታማ ሥራ የተሸጋገሩ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች የግብርናው መስክ ሽግግር አዎንታዊ ማሳያዎች መሆናቸውን አክለዋል።   ወደ ኢንቨስትመንት ከተሸጋገሩ አርሶ አደሮች መካከል አንዱ የሆኑት አቶ ኢብራሂም ከድር፤ በግብርና ሥራ በመሰማራት በሚያመርቱት ስንዴና ሌሎች ሰብሎች ውጤታማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ወደ ምርጥ ዘር ብዜት ሥራ ለመሰማራት የሚያስችል የኢንቨስትመንት መሬት ማግኘታቸውን ገልጸዋል።   ባለፉት ዓመታት በግብርና ዘርፍ ባከናወኑት ውጤታማ ሥራ ከተሰጣቸው የእውቅና ሰርተፊኬት ባሻገር በኢንቨስትመንት ማበረታቻነት ያገኙት የመሥሪያ ቦታ ለተሻለ ስራ እንደሚያነሳሳቸው የገለጹት ደግሞ አቶ በያን መሐመድ ናቸው።
በክልሉ በዘመናዊ ግብርና የእንስሳት ሀብት ምርታማነትን የማሳደግ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል 
Jul 8, 2026 157
ደሴ ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በአማራ ክልል በዘመናዊ ግብርና የእንስሳት ሀብት ምርታማነትን በማሳደግ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በምክትል ርዕስ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) ገለጹ። የክልሉ ግብርና ቢሮ "ዘመናዊ ግብርና ለሁለንተናዊ ልዕልና" በሚል መሪ ሐሳብ ያዘጋጀው የምክክር መድረክ በደሴ ከተማ ተካሒዷል።   በምክትል ርዕስ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ(ዶ/ር) እንደገለጹት፤የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ለወጭ ንግድና ለኢንዱስትሪ ግብአት የሚተርፍ ምርት ለማምረት ርብርብ እየተደረገ ነው። በዚህም በዘመናዊ አሰራር፣ የምርት ማሳደጊያ ግብአት በመጠቀም፣ በሜካናይዜሽንና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ በክልሉ በቴክኖሎጂ የተደገፈ በዘመናዊ ግብርናና እንስሳት ሀብት ልማት የተጀመረው ስራ ምርታማነትን በማሳደግ ሁለተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ መሰረት እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም በምርምር የታገዙ አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን ተግባራዊ በማድረግ ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት የሚበረታቱ ናቸው ብለዋል። አርሶ አደሩ የሚያገኘውን እርጥበት ተጠቅሞ ፈጥኖ የዘር ስራውን እንዲጀምር፣ ውሃ እንዲያሰባስብ ፣ ፈጥነው የሚደርሱና ድርቅን የሚቋቋሙ አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን እንዲጠቀም ማድረግ እንደሚያስፈልግ ነው ያመላከቱት ። ለዚህም መንግስት ምርታማነትን ለማሳደግ ቴክኖሎጂና ግብዓቶችን በስፋት እያቀረበ እንደሚገኝም ገልጸዋል።   የአማራ ክልል እንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጋሻው ሙጨ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል በጥራት እንዲመረት ከማድረግ አኳያ አበረታች የሆኑ ውጤቶች ተመዝግበዋል ብለዋል። በተለይም በሌማት ትሩፋት የወተት፣ የስጋ ፣ የእንቁላል ፣ የማር ፣ የዓሳና የሌሎችንም ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ዜጎች ጥሪት እንዲያፈሩ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ሲሉ ገልጸዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ደመቀ አድማሱ በበኩላቸው፣ በዞኑ በምርምር የወጡ አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል።   በተለይ ድርቅን የሚቋቋሙ፣ ምርታማና ፈጥነው የሚደርሱ ምርጥ ዘሮችን ለአርሶ አደሩ ለማቅረብ እንዲቻልም ሰፊ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የሰሜን ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ተገኝ አባተ በበኩላቸው፣ በተሻሻለ አሰራርና ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ንግድና ኢንቨስትመንት ፍሰትን በማሳደግ እመርታዊ ውጤት እያስገኘ ነው
Jul 7, 2026 576
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ንግድና ኢንቨስትመንት ፍሰትን በማሳደግ እመርታዊ ውጤት እያስገኘ መሆኑን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ዮሐንስ ፋንታ ገለጹ። የኢትዮጵያ ንግድ ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ከፍተኛ የኤክስፖርትና የዲፕሎማሲ ፎረም የመንግስት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ የሀገራት ዲፕሎማቶች፣ የኢትዮጵያ ላኪዎች፣ አምራቾችና ባለድርሻ አካላት መተገኙበት እየተካሄደ ነው። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ዮሐንስ ፋንታ በመድረኩ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ ተከታታይነት ያለው ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እያስመዘገበች ነው ብለዋል።   ኢትዮጵያ ለጠንካራ የንግድ ኢንቨስትመንትና ለቀጣናዊ ትስስር ማዕከል ለመሆን ምቹ ሁኔታ ያላት መሆኗን ገልጸዋል። ይህም የወጪ ንግድን ለማጠናከርና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶችን ማጠናከር ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። ዲፕሎማሲ የኢኮኖሚ ግንኙነቶችንና አጋርነት የሚጠናከርበትና ዘላቂ ልማት በተግባር የሚረጋገጥበት ስትራቴጂያዊ መሣሪያ መሆኑንም አክለዋል። በዚህም መሰረት መንግሥት ኢትዮጵያን በንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ያላትን እምቅ ሀብቶች ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የማስተዋወቅ ስራውን አጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል።   የኢትዮጵያ ንግድ ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ዋና ፀሀፊ ቀነኒሳ ለሚ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የፎረሙ ዋና ዓላማ የኢትዮጵያን የኤክስፖርት ምርቶች፣ አገልግሎቶችና የኢንቨስትመንት አማራጮች ለዓለም አቀፍ አጋሮች ማስተዋወቅ መሆኑን ተናግረዋል። መንግሥት የጀመረው የሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፉ የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ ለመዳሰስና ለባለሃብቶች ለማስተዋወቅ ፎረሙ ትልቅ ሚና እንደሚኖረው አስረድተዋል። የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት እና በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተዘጋጀው መድረክ የኢትዮጵያን ምርቶችና አገልግሎቶች በዓለም አቀፍ ገበያ ለማስተዋወቅ ጠንካራና ይበልጥ የተቀናጀ አሰራር ለመፍጠር ያግዛል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም