ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በከንቲባ አዳነች አቤቤ የተመራ ልዑክ በአዘርባጃን የተቀናጀ የከተማ ልማት ፕሮጀክትን ጎበኘ
May 20, 2026 4
አዲስ አበባ፤ግንቦት 12 /2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የተመራ የልዑካን ቡድን በአዘርባጃን ያለውን የተቀናጀ የከተማ ልማት ፕሮጀክት ጎብኝቷል። ከንቲባዋ በመልዕክታቸው፤ አዘርባጃን በአሁኑ ወቅት ካስመዘገበችው ከፍተኛ ዕድገት ጎን ለጎን የከተማ መልሶ ማልማት ሥራዎችን አጠናክራ መቀጠሏን ገልጸዋል። አሮጌ መንደሮችን በማንሳት የማደስ እንዲሁም ከዚህ ቀደም ጥቅም ላይ ያልዋሉ ቦታዎችን ለይቶ የማልማት ስትራቴጂ እየተከተለች እንደሚገኝ አመልክተዋል። በዚህም በ16 ዓመታት ጊዜ ውስጥ የሚጠናቀቁ 50 ሺህ መኖሪያ ቤቶች፣ ሆቴሎችና ተያያዥ የልማት ሥራዎች በ"Sea Breeze ፕሮጀክት" ሥር በስፋት እየተገነቡ እንደሚገኙና የግሉ ዘርፍም ከመንግሥት ጋር በመቀናጀት በከፍተኛ ደረጃ እየተሳተፈ መሆኑንም ነው ያነሱት። በአዲስ አበባም፣ በየዓመቱ 100 ሺህ ቤቶችን እና ተያያዥ ልማቶችን ለመገንባት ታቅዶ በከፍተኛ ርብርብ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ከተማ አስተዳደሩ ያረጁና የተጎሳቀሉ አካባቢዎችን የመቀየርና የማደስ ሥራዎችን እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ቀደም ሲል በአግባቡ ጥቅም ላይ ያልዋሉ እንደ የጫካ ፕሮጀክት፣ ገላን-ጉራ፣ መሐመድያ መንደር እና አዲስ ቱሞሮ ያሉ አካባቢዎችን በመጠቀም አዲስ ከተማ የመገንባት ያህል ምቹ የልማትና የመኖሪያ ስፍራዎችን ለመፍጠር እየተሠራ መሆኑን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ይህ መጠነ-ሰፊ የቤት ልማትና የከተማ ማደስ እንቅስቃሴ በዋናነት የመኖሪያ ቤት ችግርን ለማቃለልና መዲናዋን የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ የታለመ ነው ብለዋል ከንቲባዋ። በቀጣይነትም በላቀ ጥረትና በልማት ልኅቀት አዲስ አበባን እንደ ስሟ አበባ በማድረግ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ግንባር-ቀደም ለማድረግ አበክሮ የመሥራት ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አመልክተዋል።
በጋምቤላ ክልል በካሳቫና ሌሎች አዋጭ የግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፎች የተጀመሩት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
May 20, 2026 30
ጋምቤላ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ) ፡-በጋምቤላ ክልል በካሳቫና በሌሎች አዋጭ የግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፎች የተጀመሩት ተስፋ ሰጪ ስራዎች ይበልጥ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን አስታወቀ። የጋምቤላ ክልል እጅግ ሰፊና ሊታረስ የሚችል ለም መሬት፣ አመቺ የአየር ንብረት እንዲሁም ከፍተኛ ውሃ ያለው በመሆኑ ለግብርና ኢንቨስትመንት ምቹ ነው። በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በክልሉ በስፋት እየተለመደ የመጣው የካሳቫ ምርት፣ ድርቅን የመቋቋም አቅሙ ከፍተኛ በመሆኑና ለምግብ ዋስትና ከመዋሉ ባለፈ ለኢንዱስትሪ ግብዓትነት ሰፊ ፍላጎት ስላለው በክልሉ ትኩረት ከተሰጣቸው የሰብል ዓይነቶች መካከል አንዱ ነው። ክልሉ ይህንን እምቅ አቅም በመጠቀም የሃገር ውስጥና የውጭ ኢንቨስተሮችን ለመሳብ የጸጥታ ሁኔታን ከማስተካከል ባለፈ የውስጥ ለውስጥ መንገድ፣ የኤሌክትሪክና ሌሎች መሰረተ-ልማቶችን በማስፋፋት ለባለሃብቶች ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እየሰራ ይገኛል። የጋምቤላ ክልል ኢንቨስትመንት ኮሚሽን እንደገለጸው በክልሉ በባለሃብቶች የተጀመረውን ዘመናዊ የካሳቫ ልማት ወደ አርሶ አደሮች በማስፋት የምግብ ዋስትናን የማረጋገጡ ተግባር ተጠናክሮ ቀጥሏል። የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ሎው ኦቡፕ(ዶ/ር) እንዳሉት ካሳቫን ጨምሮ ለምግብ ፍጆታም ሆኑ ለገበያ አዋጭ የግብርና ኢንቨስትመንት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። የክልሉ ህዝብ ቀደም ሲል የካሳቫን ተክል እያመረተ በባህላዊ መንገድ ለምግብነት ሲጠቀም መቆየቱን አስታውሰው፤ አሁን ላይ በዘርፉ ባለሃብቶችን በማሳተፍ የካሳቫ ልማቱን ለማዘመን እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ካሳቫ ከሌሎች ስራ ስር አትክልቶች ሁሉ በምርታማነቱ ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ ተክሉ ለእንጀራና ለዳቦ ዝግጅት ከመዋሉ ባለፈ፣ ለተለያዩ የምግብ ዓይነቶች የሚያገለግል ሰብል መሆኑን ገልጸዋል። የካሳቫ ልማት በተለይም እንደ ሀገር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ለተያዘው ብሄራዊ ግብ መሳካት ዓይነተኛ ፋይዳ እንዳለውም ኮሚሽነር ሎው (ዶ/ር) ገልጸዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አቶ አንድሮው ቱት በበኩላቸው የካሳቫ ልማት በክልሉ በሚገኙ ዞኖች በባህላዊ መንገድ ሲከወን መቆየቱን ተናግረዋል። አሁን ላይ በዘመናዊ መልኩ በባለሃብት የተጀመረውን የካሳሻ ልማት ወደ አርሶ አደሩ በማስፋት እንደ ሀገር የምግብ ሎዓላዊነትን ለማረጋገጥ የታዘውን ግብ ለማሳካት በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በአቦቦ ወረዳ በካሳቫ ኢንቨስትመንት የተሰማራው የአያል ኃላፊነቱ የተወሰነ እርሻ ልማት ድርጅት ተወካይ አቶ ቾቤ ሞላ በሰጡት አስተያየት የካሳቫ ልማት በምርታማነትም ሆነ በገበያ አዋጭ ስራ መሆኑን ገልጸዋል። ካሳቫ ድርቅን የሚቋቋምና በአንድ ሄክታር መሬት ላይ ከ150 እስከ 200 ኩንታል ምርት የሚሰጥ መሆኑን ገልጸው፤ ከአራት ወር ጀምሮ ምርት መስጠት የሚችል ተክል እንደሆነ ነው የተናገሩት። ድርጅታቸው በአሁኑ ወቅት በ50 ሄክታር ማሳ ላይ ልማቱን እያከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመው በቀጣይ ዓመት ከ200 ሄክታር በላይ መሬት ልማትና የካሳቫ ዱቄት ፋብሪካ የመክፈት እቅድ ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል። የተለያዩ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ የካሳቫ ተክል ጋምቤላን ጨምሮ በደቡብና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ አካባቢዎች በአርሶ አደሮች አነስተኛ ማሳዎች ላይ እየተመረተ ለዘመናት ለምግብነት ሲያገለግል የቆየ ሰብል ነው።
በድሬደዋ አስተዳደር ባለፉት አስር ወራት ከ17ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል
May 20, 2026 78
ድሬደዋ፣ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፡- በድሬደዋ ባለፉት አስር ወራት ከ17ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የስራ ዕድል መፈጠሩን የአስተዳደሩ ስራና ክህሎት ቢሮ ገለፀ። ቢሮው በበጀት ዓመቱ በአነስተኛና ጥቃቅን ለተደራጁ ኢንተርፕራይዞች ከ112 ሚሊዮን ብር በላይ የገበያ ትስስር መፍጠሩንም ጠቁሟል። በቢሮው የስራ ዕድል ፈጠራና የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ሰኢድ አሊ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በበጀት ዓመቱ የስራ ዕድል ለመፍጠርና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ የተቀናጁ ስራዎች አበረታች ውጤቶች ተገኝተዋል። በአስተዳደሩ በተደረገው እንቅስቃሴም በበጀት ዓመቱ አስር ወራት ከ17ሺህ 300 በላይ ለሚሆኑ ከተለያዩ የትምህርት ተቋማት ለተመረቁ ወጣቶችና የህብረተሰብ ክፍሎች ቋሚ የስራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል። ለተገኘው ውጤት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ እየመጣ የሚገኘው እመርታ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን በመጠቆም። በተጨማሪም ግብርና፣ ኮንስትራክሽን እና የአገልግሎት ዘርፎች የስራ ዕድል የተፈጠረባቸው መስኮች መሆናቸውን አቶ ሰኢድ ገልጸዋል። በአስተዳደሩ የሚገኙ የተማሩ ወጣቶችን ጥያቄዎች ከአጋር አካላት ጋር በመቀናጀት የመመለስ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉንም አክለዋል። እንደ አቶ ሰኢድ ገለፃ ቢሮው በዘንድሮ በጀት ዓመት በስሩ በተደራጁት የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች በመታገዝ በአነስተኛና ጥቃቅን የተደራጁ ኢንተርፕራይዞች ውጤታማነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ድጋፎች አድርጓል። የብድር፣ አጫጭር የሙያና የክህሎት ስልጠና እንዲሁም ከሚመለከታቸው ሴክተሮች ጋር በመቀናጀት የመስሪያና የመሸጫ ቦታዎች ማመቻቸቱን ለአብነት ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ከ600 በላይ ለሚሆኑ ኢንተርፕራይዞች ከ112 ሚሊዮን ብር በላይ የገበያ ትስስር እንዲፈጥሩ በማድረግ የዕድገት ሽግግርን እንዲያፋጥኑ መሰራቱን አንስተዋል። በስራ ዕድል ፈጠራውም ሆነ በገበያ ትስስር ሴቶች እና አካል ጉዳተኞች ትኩረት ማግኘታቸውንም ገልጸዋል።
የኢንዱስትሪ ፓርኩ መገንባት መንግሥት ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት በተጨባጭ ያረጋገጠ ነው
May 19, 2026 581
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ መገንባት መንግሥት የኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሀገር ያለውን አበርክቶ ለማሳደግ በፖሊሲና በስትራቴጂ ከመደገፍ ባለፈ በተጨባጭ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳየበት መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል ገለጹ። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል ባሳለፍነው ሳምንት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተመርቆ የተከፈተውን የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክን ጎብኝተዋል። ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ መገንባት፤ መንግሥት የኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሀገር ያለውን አበርክቶ ለማሳደግ በፖሊሲና በስትራቴጂ ከመደገፍ ባለፈ በተጨባጭ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳየበት ነው። ፓርኩ በአምራች ዘርፉ ላይ የሚስተዋለውን የመሥሪያ ቦታ እጥረት በዘላቂነት ለመፍታት የማይተካካ ሚና አለው ብለዋል። አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች አቅማቸውን ገንብተው ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪነት እንዲሸጋገሩ ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ፓርኩ የተገነባበት ጥራትና የተሟላ መሠረተ ልማት የሀገር ውስጥ ምርትን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለማድረግ ያስችላል ሲሉ ገልፀዋል። የሀገር ውስጥ ምርትን በማሳደግ የገቢ ምርቶችን ለመተካት የሚደረገውን ጥረት ለሀገር ዘላቂ ሉዓላዊነት ትልቅ አስተዋፅኦ ይኖረዋል ብለዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እንዲህ አይነት ግዙፍ ፕሮጀክት መገንባቱ ትልቅ ልምድና ትምህርት የተገኘበት መሆኑን ጠቅሰው፤ ለሌሎች አካባቢዎችም እንደ ማዕከልና አርዓያ ሆኖ እንደሚያገለግል አስገንዝበዋል። በሁሉም አካባቢዎች ኢንዱስትሪን ለማስፋፋትና የሀገርን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ጉልህ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ታረቀኝ ቡሉልታ በበኩላቸው፤ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን የኢንዱስትሪ ንቅናቄን እንደሚያግዝ ገልጸው፤ ይህም የሀገር ውስጥ የገበያ ድርሻን በማሳደግ ለኢንዱስትሪዎች ጠንካራ መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል።
የሀዋሳ ከተማን ፈጣን እድገት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
May 19, 2026 378
ሀዋሳ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፡- የሀዋሳ ከተማን ፈጣን እድገት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ፡፡ ለሃዋሳ ከተማ ዘመናዊ የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ፕሮጀክት ግንባታ የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ተካሄዷል፡፡ ፕሮጀክቱን ያስጀመሩት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞና የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ (ዶ/ር) ናቸው፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በወቅቱ እንደገለጹት፤ የሃዋሳ ከተማን እድገት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ፡፡ የዚሁ አካል የሆነው የሃዋሳ ከተማ ዘመናዊ የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ግንባታ ከተማዋን ጽዱ በማድረግ የቱሪዝምና የኢንቨስመንት ማዕከልነቷን እንደሚያሳድገው አመልክተዋል። የፕሮጀክቱ ግንባታ መንግስት ለከተሞች እድገት የሰጠውን ልዩ ትኩረት እንደሚያሳይ የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል፡፡ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ (ዶ/ር) በበኩላቸው በሀገሪቱ እየታየ ያለውን ፈጣን የከተሞች እድገት የሚመጥን የፍሳሽ ቆሻሻ አስተዳደር ስርዓትና የውሃ አቅርቦትን ለማሻሻል በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በዚህም ከአለም ባንክ በተገኘ ከ775 ሚሊዮን ዶላር በላይ ድጋፍ አዲስ አበባን ጨምሮ በ23 የሀገሪቱ ከተሞች 2ኛው የከተማ የውሃ አቅርቦትና የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ፕሮጀክት ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይህም 3 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዜጎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ገልጸው ሁለት ቢሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ የሚገነባው የሃዋሳ ዘመናዊ ፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ፕሮጀክትም የዚሁ አካል ሆኖ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል ብለዋል፡፡ ፕሮጀክቱ የአካባቢ ጥበቃና ዘላቂ የፍሳሽ ቆሻሻ አወጋገድ ስርዓትን ከማጠናከር ባለፈ ፍሳሹን ለመልሶ ማልማት ስራ በማዋል ለአካባቢው ማህበረሰብ የስራ እድል ይፈጥራል ያሉት ደግሞ የክልሉ ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊ ኢንጂነር ከበደ ጋኖሌ ናቸው፡፡ ይህም በፈጣን እድገት ላይ ለምትገኘው ሃዋሳ ከተማ አለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን እንደሚጨምር ገልጸዋል፡፡ የሃዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ አገና ኔቶ በበኩላቸው ዘመናዊ የፍሳሽ ማጣሪያ ፕሮጀክቱ የሃዋሳ ከተማን ፈጣን እድገት ታሳቢ ያደረገና ሃይቋን ከብክለት የሚከላከል ነው ብለዋል፡፡
የደብረ ማርቆስ አውሮፕላን ማረፊያ ለአካባቢው ልማት፣ የቱሪዝም እንቅስቃሴና የንግድ መሳለጥ ትልቅ አቅም የሚሆን ነው
May 19, 2026 180
ደብረ ማርቆስ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ) ፡- የደብረ ማርቆስ አውሮፕላን ማረፊያ ለአካባቢው ልማት፣ የቱሪዝም እንቅስቃሴና የንግድ መሳለጥ ትልቅ አቅም እንደሚሆን ተገለጸ። የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር አመራሮችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የደብረ ማርቆስ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ አሁናዊ ሁኔታን ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ከተሳተፉት መካከል የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር የህዝብ ግንኙነት አማካሪ አበባው ግዛቸው፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ለምስራቅ ጎጃም ዞንና አካባቢው ትልቅ ብስራት መሆኑን ገልጸዋል። የአውሮፕላን ማረፊያው መገንባቱ የህዝቡን የዘመናት የልማት ጥያቄ ምላሽ የሰጠ መሆኑን አንስተው በተለይም ለቱሪዝም፣ የንግድና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል። በትራንስፖርት ዘርፉንም በማስፋት አከባቢውን ከሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች ጋር በማገናኘት የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማትን የሚያጠናክር መሆኑን አመልክተዋል። ወይዘሮ ትግስት ልየው የተባሉ የጉብኝቱ ተሳታፊ በበኩላቸው እንደገለጹት የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታው የህዝቡ የዘመናት ጥያቄ እንደነበር አውስተዋል። "አሁን ላይ በእኛ እድሜ ተገንብቶ ማየታችን አስደሳች ነው" ያሉት ወይዘሮ ትግስት ይህም ወደ አዲስ አበባና ሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች ተንቀሳቅሶ ለመስራት መልካም እድል የሚፈጥር ነው ብለዋል። ሌላው የጉብኝቱ ተሳታፊ አቶ ሙሉቀን አወቀ በበኩላቸው የደብረማርቆስ የውሮፕላን ማረፊያ መገንብቱ የአካባቢውን ልማት ከማፋጠን በተጨማሪ ምቾት ያለው ትራንስፖርት ለማህበረሰቡ ለመስጠት ያስችላል ብለዋል። በጉብኝቱ ላይ የምሥራቅ ጎጃም ዞንና የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር የመንግስት ሰራተኖችና ከከተማው የተወጣጡ የማህበረሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
አዲስ አበባ እና ባኩ የእህትማማች ከተሞች ስምምነት ተፈራረሙ
May 19, 2026 221
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ አዲስ አበባ እና ባኩ የእህትማማች ከተሞች ስምምነት ተፈራርመዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ከአዘርባጃን ዋና ከተማ ባኩ ጋር የተፈረመው ስምምነት፤ በከተማ ልማት፣ በአገልግሎት ዲጂታላይዜሽን፣ በቤት ልማት፣ በቱሪዝም (ስፖርት ቱሪዝምን) ጨምሮ በሁለቱ ህዝቦች መካከል የባህልና የታሪክ ልውውጥን የሚያጠናክር መሆኑን አመልክተዋል።
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለግብርና ቴክኖሎጂ ትኩረት ተሰጥቷል
May 19, 2026 133
ታርጫ ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልልየግብርናውን ዘርፍ በምርምር በማስደገፍ የአርሶ አደሩን ሕይወት በመሠረታዊነት ለመቀየር የተጀመረው ሥራ ውጤታማ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ በ137 ሚሊዮን ብር የተገነባውን የታርጫ ግብርና ምርምር ማዕከል ሕንጻን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። በመርሐ ግብሩ መልዕክት ያስተላለፉት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)፣ በክልሉ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለግብርና ቴክኖሎጂና ምርታማነታቸው የተረጋገጡ ምርጥ ዘሮች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ተደርገዋል ብለዋል። ዛሬ የተመረቀው የምርምር ማዕከልም የግብርናውን ዘርፍ በምርምር በማገዝ የአርሶ አደሩን ሕይወት በመሠረታዊነት ለመቀየር፣ አርሶ አደሩን የማሠልጠንና በምርምር የሚያወጣቸውን ምርጥ ዘሮች ተደራሽ ለማድረግ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ጠቁመዋል። በክልሉ የግብርናውን ዘርፍ የመልማት አቅም በምርምር በማስደገፍ ውጤታማ ለማድረግ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው ናቸው። ለዚህም የምርምር ማዕከላትን በሰው ኃይልና በግብዓት በማደራጀት ውጤታማ እንዲሆኑ ከማድረግ ጎን ለጎን ተደራሽነታቸው ላይ መሠራቱን ጠቅሰዋል። ይህም ለአርሶ አደሮች በምርምር የወጡ የግብርና ማሳደጊያዎችን በማቅረብ ምርታማነትን በማሳደግ፣ ከምግብ ፍጆታ አልፎ የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኙ ምርቶች ላይ እንዲሳተፉ እንደሚያግዝም አስረድተዋል። ምርታማነታቸው በማደጉም ራሳቸውን መጥቀምና አገርም ከዘርፉ ማግኘት የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ መሥራት ይገባል ብለዋል። የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ አማኑኤል ኃይሌ በበኩላቸው፣ የማዕከሉ መገንባት ኢንስቲትዩቱ ለሚያከናውናቸው ተግባራት ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል። ተቋሙ በሰብል፣ በእንስሳትና በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ላይ ያተኮሩ ችግር ፈቺ የምርምር ሥራዎችን በቀጥታ ወደ አርሶና አርብቶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ ሚናውን የሚወጣ መሆኑን ነው የተናገሩት። ለሕንጻ ግንባታው አጠቃላይ ከ137 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበት ገልጸው፤ ማዕከሉ የጀመራቸውን ሥራዎች አስፍቶና አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የዳውሮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ገበየሁ፣ የማዕከሉ መገንባት የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ ለአካባቢው አርሶ አደር ትልቅ ጠቀሜታ እንዳለው ጠቅሰው፣ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል። በምረቃው ሥነ-ሥርዓት የክልሉ የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ፍቅሬ አማንን ጨምሮ ሌሎች የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በከተማው በለውጡ ዓመታት የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች የህዝብን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ናቸው
May 19, 2026 79
ገንዳ ውኃ፤ ግንቦት11/2018 (ኢዜአ)--በምዕራብ ጎንደር ዞን ገንዳ ውኃ ከተማ በለውጡ ዓመታት የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች የህዝብን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ መሆናቸውን የዞኑ መስተዳድር አስታወቀ። የዞኑ መስተዳድር የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በከተማዋ የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን ተዘዋውሮ ጎብኝቷል። የምዕራብ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ በጉብኝቱ ወቅት እንደገለጹት፤ በዞኑ በለውጡ ዓመታት የህዝቡን መሰረታዊ ፍላጎቶች መሰረት ያደረጉ በርካታ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። "በገንዳ ውኃ ከተማም ሆነ እንደዞን የተገነቡና አሁንም በግንባታ ላይ ያሉ የልማት ሥራዎች የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች ውስጥ የጤና፣ የትምህርት፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ፣ የመንገድና ሌሎች የመሰረተ ልማት ሥራዎች እንደሚጠቀሱም ተናግረዋል። በቀጣይም በተገባው ቃል መሰረት ተጨማሪ የልማት ፕሮጀክቶችን በመገንባት የአካባቢውን እድገት አጠናክሮ ለማስቀጠል በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል። በጉብኝቱ ላይ የተሳተፉት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር የአስተዳደር ጉዳዮች አማካሪ አቶ ጥላሁን መኳንንት በበኩላቸው፤ በከተማዋ እየታዩ ያሉ የልማት እንቅስቃሴዎች ተስፋ ሰጪ ናቸው። በአካባቢው ሰላምን ከማስፈን ጎን ለጎን የተከናወኑ የልማት ሥራዎች በቀጣይ ዘላቂ ሰላምን በመገንባት ህዝቡን ከዚህም በላይ ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚቻል ማሳያ ናቸው ብለዋል። የተጀመሩ የተቋማት ግንባታ ሥራዎች በፍጥነትና በጥራት እንዲጠናቀቁ የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ሲሉም አረጋግጠዋል። የገንዳ ውኃ ከተማ ነዋሪ አቶ አስቻለው ጋሻው በበኩላቸው ቀደም ሲል በከተማዋ የነበሩ የመሰረተ ልማት እጥረቶች በለውጡ ዓመታት በተሰሩ ሥራዎች ከፍተኛ መሻሻል መታየቱን ገልጸዋል። በተለይም የአካባቢውን ሀብት በጥሬ እቃነት የሚጠቀም የጥጥ መዳመጫ ፋብሪካ ግንባታ ለአልሚ አርሶ አደሮችና ለሥራ ፈላጊ ወጣቶች ከፍተኛ ጥቅም የሰጠ መሆኑን አብራርተዋል። "የአካባቢያችን ሰላም በዘላቂነት በመጠበቅ ልማቱ እንዲፋጠንና ተጠቃሚነታችን እንዲያድግ የበኩላችንን እንወጣለን" ብለዋል። በእለቱ የጥጥ መዳመጫ ፋብሪካ፣ አዲስ የተገነቡ ትምህርት ቤት እና ጤና ጣቢያ፣ ሆቴል፣ የውስጥ ለውስጥ መንገድ፣ የአሚኮ ምዕራብ ጎንደር ቅርንጫፍ ግንባታና ሌሎች ተቋማት ተጎብኝተዋል።
በዞኑ የሕብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች የሚያቃልሉ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት እየተጠናቀቁ ነው
May 19, 2026 93
ጭሮ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የሕብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች የሚያቃልሉ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት እየተጠናቀቁ መሆኑን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ኢክራም ጠሀ ገለጹ። በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ጭሮ እና ሐዊ ጉዲና ወረዳዎች 950 ሚሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የመሠረተ ልማት ተቋማት በክልልና በዞን ከፍተኛ የመንግስት ሥራ ኃላፊዎች ተመርቀዋል። በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ ዋና አስተዳዳሪዋ ወይዘሮ ኢክራም ጠሀ እንዳሉት፤ መንግሥት ለሕዝብ የገባውን ቃል ወደ ተግባር በመለወጥ ሕብረተሰቡ ተጠቃሚ እንዲሆን በትኩረት እየሠራ ይገኛል። የልማት ተቋማቱን በጥራትና በፍጥነት በማጠናቀቅ የሕብረተሰቡን የረጅም ጊዜ ጥያቄዎች ለመፍታት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል በሐዊ ጉዲና የአርብቶ አደር ወረዳ ከ890 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባ የንጹሕ ውኃ ተቋም አንዱ መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ በአንድ ዓመት ተኩል ጊዜ ውስጥ ተገንብቶ የተጠናቀቀ ሲሆን፣ ከ40 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎች አገልግሎት የሚሰጥና የአርብቶ አደሩን እንስሳት የውኃ አቅርቦት ፍላጎት የሚያሟላ በመሆኑ፣ የዘመናት ጥያቄን መመለስ የቻለ መሆኑንም ተናግረዋል። ሌላው በጭሮ ወረዳ የተገነባው የመረዋ ድልድይ የአካባቢውን አርሶ አደሮች የትራንስፖርትና የቁልፍ መገናኛ ችግር ለመፍታት ታስቦ ግንባታው መከናወኑንም ጠቅሰዋል። በምረቃው ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል መሬት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ መሰረት አሰፋ በበኩላቸው፤ መንግሥት የሕዝቡን የልማት ተጠቃሚነት በማሟላት ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ የሠራቸው ሥራዎች እጅግ ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም የሕብረተሰቡን ጥያቄዎች በአጭር ጊዜ ከመመለስ ባለፈ፣ ለልማት ፕሮጀክቶች ፍጥነትና ጥራት ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ አመልክተዋል። የዞኑ አስተዳደርም የሕብረተሰቡን የልማት ጥያቄዎች በየደረጃውና በፍጥነት ለመመለስ የሚያደርገውን የተቀናጀ ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልጿል።
የአማራ ክልልን ሰላም በማስጠበቅ የተጀመሩ የልማት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ -ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)
May 19, 2026 95
ወረባቦ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፡- የክልሉን ሰላም በማስጠበቅ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን የማጠናከር ተግባር እንደሚቀጥል የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለጹ። በደቡብ ወሎ ዞን ወረባቦ ወረዳ ከ543 ሚሊዮን ብር በላይ የተገነቡ 52 የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በምረቃው ላይ ባስተላለፉት መልዕክት እንደገለፁት፣ የክልሉን ሰላም በማስጠበቅና የተጀመሩ የልማት ስራዎችን በማስቀጠል ኢትዮጵያን ተምሳሌት ሀገር የማድረጉ ተግባር ይጠናከራል። በዚህም በለውጡ መንግስት ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ የመፈጸም ብቃት ማደግ ህብረተሰቡን ፈጣን የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ችግሮችን ወደ እድልና ድል በመቀየር በልማት ስራው አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ጠቁመው፤ በክልሉ አመራሩ ከህዝቡ ጋር በመሆን እያሰፈነ ያለው ሰላምና ልማት እያረጋገጠ ነው ብለዋል። ለክልሉ ሰላቂ ሰላምና ልማት ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ጭምር በቅንጅት መስራት መቻሉ የመንግስትን አቃፊነትና አሳታፊነት የሚያረጋግጥ መሆኑን አብራርተዋል። የአማራ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱልከሪም መንግሥቱ በበኩላቸው፣ በክልሉ ለማህበራዊ ተቋማት ተደራሽነት የተሰጠው ትኩረት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው ብለዋል። በዚህም በጤናና ትምህርት ዘርፎች ህብረተሰቡን በተጨባጭ ተጠቃሚ በማድረግ አበረታችና ተስፋ ሰጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቁመው፤ ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮነን በበኩላቸው፣ ከህብረተሰቡ ጋር የዞኑን ሰላም ማስጠበቅ መቻሉ ለሚካሄዱ የልማት ስራዎች ምቹ ሁኔታ መፍጠር አስችሏል። በዚህም በዞኑ የ110 የተለያዩ ፕሮጀክቶች ግንባታን በአጭር ጊዜ በጥራት ማጠናቀቅ መቻሉን አመላክተዋል። በዛሬው እለት ብቻ በ543 ሚሊየን ብር የተገነቡ 52 የትምህርት፣ የጤና፣ የውሃና ሌሎች የልማት ፕሮጀክቶች መመረቃቸውን በማሳያነት አቅርበዋል። በተገነቡት መሰረተ ልማቶች ተጠቃሚ በመሆናቸው ተደስተናል ያሉት ደግሞ የወረባቦ ወረዳ ነዋሪዎች አቶ መሀመድ ሀሰን እና አቶ ይማም መሀመድ ናቸው። በተለይ በአጭር ጊዜ ግንባታቸው ተጠናቆ ዛሬ የተመረቁ ትምህርት ቤቶች፣ ጤና ኬላዎች፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ተጠቃሚ አድርገውናል ብለዋል።
በዞኑ በመኸር ወቅቱ በመካናይዜሽን ለታገዘ ኩታ ገጠም እርሻ ትኩረት ተሰጥቷል
May 19, 2026 97
አዳማ፣ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን በመኸር ወቅቱ የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ በመካናይዜሽን ለታገዘ ኩታ ገጠም እርሻ ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ። በዞኑ ለምርት ወቅቱ የሚያስፈልግ የምርት ማሳደጊያ ግብአትም በወቅቱ እየተሰራጨ ጥቅም ላይ እየዋለ ይገኛል። የእርሻ መካናይዜሽን የጉልበት ሥራን በሚተኩ እንደ ትራክተርና ኮምባይነር ባሉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችና ማሽኖች ግብርናን ማዘመን ሲሆን አሰራሩም ጊዜን፣ ጉልበትና ወጪን በመቀነስ የምርት መጠንንና ጥራትን በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ ነው። በዚህም መንግስት በሀገሪቱ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የመካናይዜሽን እርሻን በስፋት ለመጠቀም ግብ ጥሎ ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል። ከዚሁ ጋር በተገናኘ ኢዜአ በምስራቅ ሸዋ ዞን የ2018/19 ምርት ዘመን የመኸር ወቅት እርሻ ገጽታ በተመለከተ ከዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ጋር ቆይታ አድርጓል ። አቶ አብነት እንደገለጹት በዞኑ በመኸር ወቅቱ 512 ሺህ 622 ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ ሰብሎችን በማልማት ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ተግባራዊ እየተደረገ ነው። በምርት ወቅቱ የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ በመካናይዜሽን ለታገዘ ኩታ ገጠም እርሻ ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል። በዚህም በምርት ወቅቱ አጠቃላይ ከሚለማው መሬት ውስጥ ከ410 ሺህ ሄክታር በላይ በኩታ ገጠም እንደሚለማ ገልፀው እስካሁን ድረስ ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በትራክተር በመታገዝ መታረሱን ተናግረዋል። በዞኑ ከሚያዚያ 2018 ዓ.ም መጨረሻ አንስቶ የአገዳ ሰብሎችን መዝራት እየተካሄደ መሆኑን ጠቅሰው በሰኔ 2018 ዓ.ም ደግሞ የብርእ ሰብሎች በስፋት እንደሚዘሩ አመልክተዋል። በመኸር ወቅት እርሻው ከ195 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ መሆናቸውን ጠቅሰው በምርት ወቅቱ የተያዘውን ግብ ለማሳካት በየደረጃው የሚገኙ አመራሮችና የግብርና ባለሙያዎች ለአርሶ አደሩ የቅርብ ክትትልና ድጋፍ እያደረጉ መሆናቸውን አውስተዋል። የምስራቅ ሸዋ ዞን ህብረት ስራ ማህበራት ማስፋፊያ ፅህፈት ቤት ሃላፊ አቶ አስራት ጌቱ በበኩላቸው በምርት ዘመኑ ለዞኑ ከሚያስፈልገው አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ዳፕና ዩሪያ ማዳበሪያ ውስጥ ከ900 ሺህ ኩንታል በላይ የሚሆነው መቅረቡን ተናግረዋል። እስካሁን ድረስ 537 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ በህብረት ስራ ማህበራት በኩል ለአርሶ አደሮች መሰራጨቱን ጠቁመው አርሶ አደሮችም ማዳበሪያን በመጠቀም የግብርና ስራቸውን እያሳለጡ ይገኛሉ ብለዋል። በተጨማሪም ጤፍና ስንዴን ጨምሮ ከ68 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑን አስታውቀዋል።
ጉምሩክ ኮሚሽን አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድን በመከላከል ከፍተኛ ሚናውን እየተወጣ ነው
May 19, 2026 201
አዲስ አበባ፤ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ ጉምሩክ ኮሚሽን ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድን መከላከል እና የገቢ አሰባሰብን የሚያዛቡ የተጭበረበሩ ሰነዶችን መቆጣጠር የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም በተቋም ግንባታ የፋና ወጊነት ሚና እየተወጣ መሆኑን የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የፌደራል መንግሥት አስፈፃሚ አካላትን ሥልጣንና ተግባር ለመወሰን በወጣው አዋጅ ቁጥር 1097/2011 መሰረት የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡ በዚህም ሀገራዊ ሪፎርሙን ተከትሎ ተቋማዊ ሪፎርም በማድረግ ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድን መከላከል፣ የገቢ አሰባሰብን ማሳደግ የሚያስችል አደረጃጀት ፈጥሯል፡፡ የጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ተቋሙ በአዋጅ ከተሰጠው ቁልፍ ተልዕኮዎች መካከል ከገቢና ወጭ እቃዎች ታክስን አስልቶ ገቢ መሰብሰብ ነው፡፡ ሀገራዊ ሪፎርሙን ተከትሎ በተደረገው የተቋም አደረጃጀት ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድን መከላከል የሚያስችሉ ግልጽ የህግ ማዕቀፎች ተዘጋጅተዋል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ከሪፎርሙ በፊት በ2011 በጀት ዓመት የተሰበሰበው ገቢ 78 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር እንደነበር ገልጸው፤ በተያዘው በጀት ዓመት አስር ወራት ከታቀደው በላይ 600 ነጥብ 23 ቢሊየን ብር በላይ ጥቅል ገቢ ተሰብስቧል ብለዋል፡፡ ሪፎርሙ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም፣ ህጎችን በማሻሻልና አሰራርን በማዘመን የገቢ አሰባሰብ፣ የህገ ወጥና ኮንትሮባንድን መከላከል የሚያስችል አቅም መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡ ኮሚሽኑ ዕቃዎችን ከአደጋ በመከላከል ደህንነታቸው ተጠብቆ ከመዳረሻ ቦታቸው እንዲደርሱ የሚያስችል የኤሌክትሮኒክ ካርጎ ትራኪንግ ቴክኖሎጂ ሥራ ላይ አውሏል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ወደ ውጭ በምትልካቸው እቃዎች በመንገድ ላይ ይደርስ የነበረውን መዘግየት፣ ቅሸባና ስርቆት እና መሰል ችግሮች እንዳይከሰቱ መቆጣጠር የሚያስችል ቴክኖሎጂ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ በቴክኖሎጂ የታገዘ የተቀናጀ የድንበር ቁጥጥር ስርዓት በመዘርጋት የካርጎ እንቅስቃሴዎችን ማዕከል ላይ ሆኖ መቆጣጠር የሚቻልበት ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ የተገልጋይ መንገደኞችን እንቅስቃሴ በመቆጣጠር ህገ ወጥ እንቅስቃሴን መከላከልና መቆጣጠር የሚያስችል ቴክኖሎጂ ጥቅም ላይ መዋሉን ገልጸዋል፡፡ ኮሚሽኑ ሪፎርሙ በፈጠራቸው መልካም ዕድሎች ዘመናዊና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት በኢትዮጵያ የተቋማት ግንባታ ፋና ወጊ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በርካታ ቴክኖሎጂዎች ሥራ ላይ መዋላቸውን ገልጸው፤ የማንዋል አሰራርን በማስወገድ ለአምራቾች፣ አስመጭዎችና ላኪዎች የተሳለጠ አገልግሎት እየሰጡ ነው ብለዋል፡፡ የኦን ላይን አገልግሎቶችን በመስጠት የተገልጋዮችን ጊዜና ጉልበት ይቀንሳል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ቴክኖሎጂዎች ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድ መከላከል እና የገቢ አሰባሰብን የሚያዛቡ የተጭበርበሩ ሰነዶችን መቆጣጠር እንዳስቻሉ ገልጸዋል፡፡ ይህም የማንዋል አሰራሮችን በማስቀረት ብልሹ አሰራርን በማስወገድ ኮሚሽኑ ተልዕኮውን በብቃት እንዲወጣ ማስቻሉን ተናግረዋል።
የንብ ሃብት ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ከማሳደግ ባለፈ የሥራ እድል እየፈጠረ ነው
May 19, 2026 128
ዲላ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦የንብ ሃብት ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ከማሳደግ ባለፈ የሥራ እድልን በመፍጠር ረገድ ያለው ድርሻ መጨመሩ ተመላከተ። ዓለም አቀፍ የንብ ቀን በክልል ደረጃ በዲላ ከተማ በተለያዩ ሁነቶች እየተከበረ ነው። በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትንና ዓሣ ሀብት ልማት መሪ ሥራ አስፈፃሚ አቶ አዚዝ አያሌው በወቅቱ እንዳሉት፤ ንብ ከማር ምርት ባሻገር የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግና የተፈጥሮ ሚዛንን ለመጠበቅ ሚናዋ የጎላ ነው። የንብን ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ለማስፋት በተደረገ ጥረት ልማቱ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ከማሳደግ ባለፈ የሥራ እድልን በመፍጠር ረገድ ያለው ድርሻ መጨመሩን አመልክተዋል። አምራችና አቅራቢዎችን ጨምሮ ባለድርሻ አካላትን በማቀራረብና በማቀናጀት የዘርፉን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ የንብ ሃብት ልማት አማራጭ የሥራ እድል ፈጠራ ምንጭ በመሆን የአምራቹን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ መቻሉን ያነሱት ደግሞ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ በቢሮ ኃላፊ ማዕረግ የዲላ ክላስተር ማስተባበሪያ አማካሪ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አበባየሁ ኢሳያስ ናቸው። በተለይ የተራቆቱ ተራራዎችን በተፋሰስ በማልማት ለንብ ሃብት ልማት መዋሉንና በዚህም 125 ኢንተርፕራይዞች እና በዘርፉ ሦስት ዩኒየኖችን ወደ ሥራ ማስገባት መቻሉን ገልጸዋል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ከ200 በላይ እጽዋቶችን ያቀፈው የጌዴኦ መልክዓ ምድር ለንብ ሃብት ልማት ምቹ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ በንብ ሃብት ልማት ያለውን ጸጋ ለመጠቀም በተለይ ዝቅተኛ የእርሻ መሬት ላላቸው አርሶ አደሮች የግብዓትና የሙያ ድጋፍ በመስጠት ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉን አንስተዋል። በዚህም በዓመት ከ4 ሺህ ቶን በላይ የተጣራ ማር ለገበያ ከማቅረብ ባለፈ በቡና ተፈጥሯዊ ማር አለም አቀፍ እውቅና በማግኘት ለውጭ ገበያ እየቀረበ ነው ብለዋል። ዓለም አቀፉ የንብ ቀን በፓናል ውይይት፣ በማር ኤግዚቢሽንና በተለያዩ ሁነቶች እየተከበረ ይገኛል።
በክልሉ የቱሪዝም ሀብቶችን ለይቶ ጥቅም ላይ ለማዋል የተሰሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል
May 19, 2026 121
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ያሉ የቱሪዝም ሀብቶችን በመለየት፣ በማልማትና ለጎብኚዎች ምቹ በማድረግ ረገድ በተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ባለፉት ዓመታት የለውጡ መንግስት እንደ ሀገር ተግባራዊ ያደረገው የብዝሃ-ዘርፍ ኢኮኖሚ ግንባታ ፖሊሲ በኢትዮጵያ ለዓመታት ሳይታወሱና ሳይለሙ የቆዩ እምቅ የተፈጥሮና የሰው ሰራሽ ጸጋዎችን አውጥቶ ጥቅም ላይ ለማዋል አስችሏል። የተፈጥሮ ጸጋዎችን ለማልማት በተከናወኑ የተቀናጁ ተግባራትም ተጨባጭና ስኬታማ ውጤት እየተመዘገበ ነው። ኢኮኖሚውን ከአንድ ዘርፍ ጥገኝነት ለማውጣት በተነደፈው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ዕቅድ ውስጥ ቱሪዝም አንዱና ዋናው የኢኮኖሚ ምሶሶ ተደርጎ ትኩረት ተሰጥቶታል። በሀገሪቱ ዕምቅ የቱሪዝም ሀብቶች ከሚገኙባቸው አካባቢዎች መካከል ደግሞ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አንዱ ሲሆን ክልሉ ሀብቶቹን ወደ ውጤት በመቀየር ረገድ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራትን በማስመልከት ኢዜአ ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ጋር ቆይታ አድርጓል። ርዕስ መስተዳድሩ አቶ ጥላሁን ከበደ እንዳሉት፤ በክልሉ የሚገኙ ዕምቅ የቱሪዝም ሀብቶች ተለይተው እንዲተዋወቁና የልማቱ አካል እንዲሆኑ ሀገራዊ ለውጡ ምቹ መደላድል ፈጥሯል። ቀደም ሲል ለቱሪዝም ዘርፍ ብዙም ትኩረት ባለመሰጠቱ ኢኮኖሚያዊ አስተዋፅኦው የጎላ እንዳልነበር አስታውሰው፣ ለውጡን ተከትሎ በተሰጠ ትኩረት በክልሉ ያሉ የቱሪስት ሀብቶችን ለይቶ የማልማትና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የማሳደግ ሥራ መሰራቱን ተናግረዋል። እንደ ሀገር ለቱሪዝም ዘርፍ እየተሰጠ ያለው ትኩረት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣት በክልሉ የቱሪዝም ልማት ላይም የራሱን አበርክቶ ማድረጉን አቶ ጥላሁን ገልጸዋል። በክልሉ የበርካታ ብሔር ብሔረሰቦች ባህላዊ እሴቶች እንዲሁም ሀይማኖታዊና ታሪካዊ ስፍራዎች እንዳሉ ገልጸው፣ እነዚህ የቱሪዝም ሀብቶች ለኢኮኖሚው እድገት አስተዋፅኦ እንዲኖራቸው በልዩ ትኩረት ሲሰራ ቆይቷል ብለዋል። በዚህም በክልሉ ከዘርፉ የሚገኘው ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እያደገ መምጣቱን ጠቁመው፣ በቀጣይም ይህን ውጤት በማስቀጠል የዘርፉን ፋይዳ ለማሳደግ ይሰራል ብለዋል። እንደ ርዕሰ መስተዳድሩ ገለጻ፣ በክልሉ የመስህብ ስፍራዎችን የማልማትና የማስተዋወቅ እንዲሁም የመጠበቅ ሥራዎች በቅንጅት እየተከናወኑ ሲሆን ይህም የጎብኚዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እንዲጨምር አድርጓል። ባለሀብቶችም ትልልቅ ሆቴሎችን ጨምሮ ደረጃቸውን የጠበቁ አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን በመገንባት በቱሪዝም ዘርፉ ክልሉም ሆነ ሀገር ተጠቃሚ እንዲሆኑ የራሳቸውን አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ ያለፉት ዘጠኝ ወራት በክልሉ ያሉ የቱሪስት መስህቦችን ከጎበኙ ከ43 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር ጎብኚዎች 480 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱንም ለማወቅ ተችሏል።
በአፋር ክልል የተለያዩ ወረዳዎች የተገነቡ የመጠጥና የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ
May 19, 2026 128
ሰመራ ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦በአፋር ክልል የተለያዩ ወረዳዎች የተገነቡ የመጠጥና የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ። ፕሮጀክቶቹን መርቀው ስራ ያስጀመሩት የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እና የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) ናቸው። የተመረቁት ፕሮጀክቶች ነዋሪዎች ከዚህ ቀደም ይገጥማቸው የነበረውን የመጠጥ ውሃ ችግር በዘላቂነት የሚፈቱ መሆኑ ተመላክቷል። በተለይም አርብቶ አደሮች ውሃ ለማግኘት ሩቅ አካባቢዎች በመሄድ ይደርስባቸው የነበረውን እንግልት የሚያስቀር መሆኑም ታውቋል። የመስኖ ፕሮጀክቱም የክልሉ አርብቶና አርሶ አደሮች በአካባቢው ያለውን ሰፊ መሬት በማልማት ምርታማ እንዲሆኑ የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። በመርሃ ግብሩ ላይ የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እና የመስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) እና ሌሎችም የፌዴራልና የክልሉ የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል።
የመንገዱ መገንባት ቀደም ሲል ሲገጥመን የነበረን እንግልት አስቀርቶልናል - ነዋሪዎች
May 19, 2026 161
ቦንጋ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በአካባቢያቸው ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው መንገድ ቀደም ሲል ሲገጥማቸው የነበረውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር ማስቀረቱን በኮንታ ዞን የኮንታ ኮይሻ ወረዳ ነዋሪዎች ተናገሩ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት በወረዳው የድልቢ ቀበሌ ነዋሪ አቶ በቀለ በተላ እና አቶ ብቸራ ቡሽራ ከዚህ ቀደም በአካባቢው መንገድ ባለመኖሩ ወደ ተለያዩ አካባቢዎች ለመንቀሳቀስ ይቸገሩ ነበር። በመንገድ እጦት ሕሙማንንም ሆኑ ነፍሰጡር እናቶችን ወደ ሕክምና ተቋም ለማድረስ እንዲሁም የግብርና ምርታቸውን ለገበያ ለማቅረብ ይቸገሩ እንደነበርም አስታውሰዋል። አሁን ላይ በአካባቢያቸው ተገንብቶ ለአገልግሎት የበቃው መንገድም ችግሩን መፍታቱን ጠቁመዋል። የመንገዱ ግንባታ ለፀጥታ ሥራ ትልቅ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ያነሱት ደግሞ ዋና ኢንስፔክተር ጊዲሶ አመሌ፣ በተለይ ችግሮች ሲከሰቱ ፈጥኖ ቦታው ደርሶ ምላሽ ለመስጠት እንዳስቻለም ተናግረዋል። ወይዘሮ ጤናዬ ሹምቡል በበኩላቸው፤ የመንገዱ አገልግሎት መጀመር በተለይ ሴቶችና ተማሪዎች ላይ ሲገጥም የነበረን ችግር ማስቀረቱን ጠቁመው፣ ወላድ እናቶች ወደጤና ተቋማት ሄደው እንዲወልዱ ማስቻሉን ገልጸዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ምክትል ሀላፊ ኢንጂነር ጌዲዮን እስጢፋኖስ፣ የክልሉ መንግስት የማህበረሰቡን የመንገድ መሰረተ ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ቀበሌን ከቀበሌ እና ከዋና መንገድ የማገናኘት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። በዓለም ባንክ ድጋፍ የገጠር ትስስር ለምግብ ዋስትና ፕሮግራም በ6 ዞኖች ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች በ865 ሚሊዮን ብር የመንገድ ግንባታ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል። ሰሞኑን ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው የ12 ኪሎ ሜትር ደልባ-አልፋ-ቶልካ መንገድ ፕሮጀክት አንዱ መሆኑንም ጠቅሰዋል። መንገዱ ከሦስት በላይ ቀበሌዎችን እርስ በርስ የሚያገናኝና ከ52 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበትም ተናግረዋል። የመንገዱ መገንባት ከዚህ ቀደም በአካባቢው ማህበረሰብ ላይ ይደርስ የነበረውን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሌሎች ችግሮችን መፍታቱንም ኢንጂነር ጌድዮን ተናግረዋል።
በሀገራት መካከል የሚፈጠር ጠንካራ የኢኮኖሚ ትስስር አስተማማኝና ዘላቂ መረጋጋትን ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አለው
May 18, 2026 516
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦በሀገራት መካከል የሚፈጠር ጠንካራ የኢኮኖሚ ትስስር አስተማማኝና ዘላቂ መረጋጋትን ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳለው የጅቡቲ የኢኮኖሚ፣ ፋይናንስ፣ ኢንዱስትሪና ፕላኒንግ ሚኒስትር ኢልያስ ሙሳ ገለጹ። በሶማሌ ክልል ርዕሰ መዲና ጅግጅጋ ከተማ በቀጣናው ሰላም እና ደኅንነት ላይ ትኩረቱን ያደረገ ከፍተኛ ቀጣናዊ ፎረም እየተካሄደ ይገኛል። ’’ቀጣናዊ ተቋማትን ማጠናከር ለአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ ሰላም መረጋገጥ” በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀው ፎረም ቀጣናዊ መፍትሄዎች ለቀጣናዊ ችግሮች የሚለውን ዕሳቤ ማስተዋወቅ ዋና ዓላማው አድርጓል። ይህ መድረክ በውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት፣ በሰላም እና ፖለቲካዊ ምክክር ማዕከል፣ በሶማሌ ክልል መንግስትና ሌሎች አጋር አካላት በጋራ ተዘጋጅቷል። በጅግጅጋ ከተማ በተዘጋጀው ፎረም ላይ የኢትዮጵያን ጨምሮ የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት መንግስታት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ ምሁራን፣ ባለድርሻ አካላትና ተጋባዥ እንግዶች ታድመዋል። የጅቡቲ የኢኮኖሚ፣ ፋይናንስ፣ ኢንዱስትሪና ፕላኒንግ ሚኒስትር ኢልያስ ሙሳ፤ ጅቡቲና ኢትዮጵያ ከፍተኛ የንግድ ትስስር ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን አስታውሰው፤ በሀገራት መካከል የሚፈጠር ጠንካራ የኢኮኖሚ ትስስር አስተማማኝና ዘላቂ መረጋጋትን ለመፍጠር ትልቅ ማበረታቻ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ አካያ ለቀጣናዊ ብልፅግና እና ቀጣናዊ ሚዛንን ለመጠበቅ የኢትዮጵያ ሚና ታላቅ፣ ወሳኝና የማይተካ መሆኑን አክለዋል። የቀጣናዊ ራዕዩ ዋና ማዕከል የኢኮኖሚ ትስስር እና የኢኮኖሚ ኮሪደሮች መሆን እንዳለባቸውም ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ በኃይል ትስስር ረገድ ያሳየችውን ታላቅ መሪነትና የተግባር አፈጻጸም ያደነቁት ሚኒስትሩ፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ እና የፋይበር ኦፕቲክ የቴሌኮም መሠረተ ልማቶች የሁለቱን ሀገራት ኢኮኖሚና ህዝቦች በማገናኘት ረገድ ያላቸውን ጉልህ ሚና ገልጸዋል። በቀጣናው መጪው ጊዜ በጥንካሬ እንዲቃኝ፤ በጋራ ኃላፊነት፣ በኢነርጂ እንዲሁም በመሠረተ ልማት ትስስር ላይ የተመሰረተ ቀጠናዊ ትብብር መገንባት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ ቀጣናው የጋራ ውሳኔዎችን የሚያሳልፍበትና በተግባር ላይ ያተኮረ ትብብር የሚያመነጭበት ጠንካራ መድረክ እንደሚያስፈልገው በማሳሰብ፥ ጅቡቲ በአፍሪካ ቀንድ ሀገራት መካከል የሚደረጉ ውይይቶች ተቋማዊ ቅርፅ እንዲይዙ ሙሉ ድጋፏን እንደምትሰጥ አረጋግጠዋል።
ዘላቂ ሰላም በማስፈን የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ የቀጣናውን ተቋማት ቅንጅታዊ አሠራር ማጠናከር ይገባል
May 18, 2026 320
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦በምሥራቅ አፍሪካ ዘላቂ ሰላም በማስፈን የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ የቀጣናውን ተቋማት ቅንጅታዊ አሠራር ማጠናከር እንደሚገባ በኬንያ የጋሪሳ ካውንቲ ግዛት ገዥ ናቲፍ ጃማ አደም ገለጹ። በሶማሌ ክልል ርዕሰ መዲና ጅግጅጋ ከተማ በቀጣናው ሰላም እና ደኅንነት ላይ ትኩረቱን ያደረገ ከፍተኛ ቀጣናዊ ፎረም እየተካሄደ ይገኛል። ’’ቀጣናዊ ተቋማትን ማጠናከር ለአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ ሰላም መረጋገጥ” በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀው ፎረም ቀጣናዊ መፍትሄዎች ለቀጣናዊ ችግሮች የሚለውን ዕሳቤ ማስተዋወቅ ዋና ዓላማው አድርጓል። ይህ መድረክ በውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት፣ በሰላም እና ፖለቲካዊ ምክክር ማዕከል፣ በሶማሌ ክልል መንግስትና ሌሎች አጋር አካላት በጋራ ተዘጋጅቷል። በጅግጅጋ ከተማ በተዘጋጀው ፎረም ላይ የኢትዮጵያን ጨምሮ የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት መንግስታት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ ምሁራን፣ ባለድርሻ አካላትና ተጋባዥ እንግዶች ታድመዋል። የጋሪሳ ካውንቲ ግዛት ገዥ ናቲፍ ጃማ አደም በመድረኩ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ የምክክር ፎረሙ ወቅታዊና እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው፣ በምሥራቅ አፍሪካ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን ቀጣናዊ ተቋማትን ማጠናከር ቀዳሚ ተግባር መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። የምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና በተለያዩ ተፈጥሯዊ ጸጋዎች የታደለ፣ ስትራቴጂካዊ መልክዓ-ምድር ያለው እንዲሁም አፍሪካን ከመካከለኛው ምሥራቅና እስያ ጋር የሚያገናኘው የዓለም ትልቁ የባህር ላይ ንግድ መስመር መገኛ መሆኑን ገልጸዋል። ቀጣናው እምቅ የተፈጥሮ ሀብት፣ የበለጸገ ብዝኃ ባህልና ሰፊ የእንስሳት ሀብት ያለው ቢሆንም፤ ግጭት፣ የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ ድርቅና መፈናቀል ተደጋጋሚ ፈተናዎቹ ሆነው መቀጠላቸውን ገዥው ጠቁመዋል። ምሥራቅ አፍሪካ የዕውቀት፣ የተፈጥሮ ሀብት አልያም የአመራር እጥረት የለበትም ያሉት ናቲፍ ጃማ፤ በአሁኑ ወቅት የጎደለው የተቀናጀ የፖለቲካ አመራርና ቀጣናዊ እሳቤ መሆኑን አስገንዝበዋል። ይህንን ችግር ለማቃለል የአየር ንብረት ተጋላጭነትን በጋራ መከላከል፣ ድንበር ተሻጋሪ የአርብቶ አደሮችን እንቅስቃሴ በቅንጅት መምራት እና የቀጣናዊ መሠረተ ልማት ኮሪደርን ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። በቀጣናው በአንድ ሀገር የሚከሰት ግጭትና አለመረጋጋት በቅጽበት በጎረቤት ሀገራት ላይ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር የጠቀሱት ገዥው፤ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ከንግግር የዘለለ የተቋማት መዋቅራዊ ትስስርና ቅንጅታዊ አሠራር መፍጠር እንደሚገባ አሳስበዋል።
በክልሉ ገበያን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
May 18, 2026 198
ደብረ ማርቆስ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑ ተመለከተ። በደብረ ማርቆስ ከተማ ከ230 ሚሊየን ብር በላይ ወጭ የተገነባ የገበያ ማእከል ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል። በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማእረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳሃሉ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ በክልሉ ገበያን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ምርታማነትን የማሳደግ፣ የግብይት ስርአቱን የማሳለጥ፣ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ የማገናኘትና ህገ ወጥ ደላሎች ላይ ቁጥጥር የማጠናከር ተግባራት እየተከናወኑ ነው። በደብረ ማርቆስ ከተማ የተገነባው የገበያ ማእከል የጥረቱ አንድ አካል መሆኑን ጠቁመው ማእከሉ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ግብይቱን በማሳለጥ በኩል ሚናው የጎላ መሆኑን አመልክተዋል። የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር በዚህ በኩል እያደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን ጠቁመው በቀጣይም አስተዳደሩ በዘርፉ ለሚያከናውናቸው ተግባራት ድጋፍ እንደሚደረግ አስታውቀዋል። የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ተሾመ ዋለ በበኩላቸው፤ የገበያ ማእከሉ አምራቹና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመገበያየት የሚያስችል ነው ብለዋል። ማእከሉ ለከተማዋ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑንም አስታውቀዋል። የከተማ አስተዳደሩ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ ዮሴፍ መለሰ በበኩላቸው፤ የገበያ ማእከሉ ከ230 ሚሊየን ብር በላይ ወጭ የተገነባ መሆኑን ተናግረዋል። ማእከሉ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች የሚገበያዩበት በመሆኑ ለሸማቹ ህብረተሰብ የሚያስገኘው ጥቅም ከፍተኛ መሆኑን አስረድተዋል። የገበያ ማእከሉ መገንባት የንግድ ስርአቱን ለማዘመን የሚደረገውን ጥረት ያግዛል ያሉት ደግሞ የከተማው ንግድና ዘርፍ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሙሉጌታ አስረስ ናቸው። በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።