ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በኢሉአባቦር ዞን በቴክኖሎጂ የታገዘ ግብርናን በማስፋፋት ምርታማነትን ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ ነው
May 25, 2026 89
መቱ፣ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ):- በኢሉአባቦር ዞን በቴክኖሎጂ የተደገፈ ግብርናን በማስፋፋት ምርታማነትን ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በዞኑ በክረምት እርሻ ከ389 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች የመሸፈን ስራም ተጀምሯል። በክረምት እርሻው በቆሎ፣ ማሽላ፣ ሩዝ፣ አኩሪ አተርና ሌሎች የሰብል ዓይነቶች የሚዘሩ ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው መሬት በኩታ ገጠም የሚታረስ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳሙ ታከለ ተናግረዋል። ምርታማነትን ለማሳደግም በኩታ ገጠም የማረስ ልማድን በማዳበር እንዲሁም በማዳበሪያና የምርጥ ዘር አቅርቦት ላይ በትኩረት መሰራቱን ኃላፊው ገልጸዋል። ለዚህም ከ161 ሺህ ኩንታል በላይ የኬሚካል ማዳበሪያ እና ከ24 ሺህ ኩንታል በላይ የተለያዩ ምርጥ ዘሮች በክረምት እርሻው በስራ ላይ እንደሚውሉ አስታውቀዋል። ከዚህ ውስጥ 61 ሺህ ሔክታር መሬት በበቆሎ ሰብል የሚሸፈን ሲሆን፤ ለዚሁ ተግባር የሚሆን ከ50 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ መቅረቡንም አክለው ገልጸዋል። በሌላ በኩል በዞኑ ስር በሚገኘው የያዮ ወረዳ በክረምት እርሻ ከ11 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች የመሸፈን ስራ እየተከናወነ መሆኑን የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ በፈቃዱ ኦልጂራ ገልጸዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ ግብርናን በማስፋፋትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። አርሶ አደሮችም በኩታ ገጠም በማረስ ምርታማነታቸውን ለማሳደግ፣ የምግብ ዋስትናቸውንና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ለክረምት እርሻው ከፍተኛ ትኩረት መስጠታቸውን ተናግረዋል። በያዮ ወረዳ የአጪቦ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ጌታቸው በቀለ፣ አርሶ አደር ተስፋዬ ሀብተማርያም እና አርሶ አደር ብርሃኔ አሰፋ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በኩታ ገጠም ከ116 ሔክታር በላይ መሬት ላይ በቆሎ መዝራት መጀመራቸውን ገልጸዋል። አርሶ አደሮቹ የማሳ ዝግጅት ስራቸውን ቀደም ብለው በማከናወናቸው እንዲሁም የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ አቅርቦትም ቀድሞ በመድረሱ ማሳቸውን በዘር የመሸፈን ተግባርን ቀድመው መጀመራቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም የግብርና ስራቸውን በቴክኖሎጂ ለመደገፍ በትራክተር የማረስ ስራ እንዲያከናውኑ በወረዳው አስተዳደር በኩል አስፈላጊው እገዛ እንደተደረገላቸውም ገልጸዋል።
ለዒድ አል-አድሃ (ዓረፋ) በዓል የምርት እጥረት እንዳያጋጥም ዝግጅት ተደርጓል-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 25, 2026 155
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ለ1447ኛ ጊዜ የሚከበረውን የዒድ አል-አድሃ (ዓረፋ) በዓል ምክንያት በማድረግ ነዋሪዎቻችን በዓሉን ያለምንም የገበያ ጫና እና እንግልት በደስታ ማክበር እንዲችሉ፣ መሰረታዊ የፍጆታ ዕቃዎች እና የበዓል ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እና በበቂ መጠን እንዲቀርቡ ሰፊ ዝግጅት መደረጉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። በተለይም በከተማችን በሚገኙ 7ቱም የግብርና ምርቶች መሸጫ ማዕከላት የሰብል፣ የጥራጥሬ፣ የአትክልትና የፍራፍሬ ምርቶች በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ ቀርበው ይገኛሉ ብለዋል። ሸማቾች በቀላሉ በአቅራቢያቸው መገብየት እንዲችሉ በሁሉም አካባቢዎች የሚገኙ 250 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች እስከ በዓሉ ዋዜማ ድረስ ክፍት ሆነው እንዲሰሩ ተደርጓል። በ2 ሺህ 52 የሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት ሱቆች እና በአዲስ አበባ ንግድ ስራዎች ድርጅት መጋዘኖች አማካኝነት የዘይት እና የዱቄት ምርቶች በበቂ መጠን ተደራሽ ሆነዋል። በመሆኑም የከተማችን ነዋሪዎች ከተጠቀሱት የገበያ አማራጮች በአቅራቢያችሁ ከሚገኙት መጠቀም ትችላላችሁ ሲሉ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ጠቁመዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ የሚያግዙ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተከናወነ ነው
May 25, 2026 217
ደሎ መና፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ የሚያግዙ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል የመስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ሮባ ቱርቼ አስታወቁ። በባሌ ዞን ደሎ መና ወረዳ ከ936 ሚሊየን ብር በሚልቅ ወጪ የተገነባው የያዶት የመስኖ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል። ፕሮጀክቱ የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ከመቀነስ ባለፈ፤ ለእንስሳት የመጠጥ ውኃ አገልግሎት የሚውል መሆኑም ተመላክቷል። አቶ ሮባ ቱርቼ በምረቃው ወቅት እንዳሉት፤ የክልሉ መንግሥት የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ትርጉም ባለው መልኩ ለመቀነስ የሚያግዙ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ ላይ በትኩረት እየሠራ ይገኛል። መንግሥት የአርብቶ አደሩ ማኅበረሰብ በተደጋጋሚ ጊዜ የሚያጋጥመውን ድርቅ እንዲቋቋም በክልል ደረጃ ከ166 የሚበልጡ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶችን አጠናቆ ለአገልግሎት አብቅቷል ብለዋል። ከተጠናቀቁት የመስኖ ፕሮጀክቶች መካከል 66 የሚሆኑት ለሰውና ለእንስሳት መጠጥ ጭምር አገልግሎት የሚውሉ መሆናቸውንም አስረድተዋል። በዛሬው ዕለት ለምረቃ የበቃው የያዶት የመስኖ ፕሮጀክት ከ3 ሺህ ሔክታር የሚበልጥ መሬት በማልማት ከ6 ሺህ በላይ አባወራዎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። የባሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሀኪም አልይ በበኩላቸው፤ በዞኑ ቆላማ አካባቢዎች የተገነቡ የመስኖ ፕሮጀክቶች የአርብቶ አደሩን ኑሮ በማሻሻል በኩል ከፍተኛ ውጤት እያመጡ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ ከ1 ሺህ 700 የሚበልጡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ከ4 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ ተገንብተው እየተመረቁ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይም ኅብረተሰቡን በቀጥታ ተጠቃሚ ለሚያደርጉ ፕሮጀክቶች ቅድሚያ እንደሚሰጥ አመላክተዋል። የክልሉ መንግሥት የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለሚያረጋግጡ የልማት ፕሮጀክቶች ልዩ ትኩረት መስጠቱን ያረጋገጡት ደግሞ በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ መንግሥቱ በቀለ (ዶ/ር) ናቸው። የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የቆላማና ዝናብ አጠር አካባቢዎች ዘላቂ ልማት ዕቅድ በመንደፍ የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቋቋም በትጋት እየተሠራ ነው ብለዋል። በቀጣይም የክልሉ መንግሥት ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ለውጤት በማብቃት የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልጿል።
በክልሉ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የሕብረት ሥራ ማህበራትን የማብቃት ሥራው ይጠናከራል-እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
May 25, 2026 116
ሆሳዕና፣ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የሕብረት ሥራ ማህበራትን ደግፎ የማብቃት ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። ርዕሰ መስተዳድሩ በሀድያ ዞን ሊቻ ሁለገብ የገበሬዎች ሕብረት ሥራ ዩኒየን የወተት ማምረቻ፣ ማቀነባበሪያና ግብይት ማዕከልን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት፥ በክልሉ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የሕብረት ሥራ ማህበራትን ደግፎ የማብቃት ጅምሩ ተጠናክሮ ይቀጥላል። በክልሉ የሕብረት ሥራ ማህበራት በምርጥ ዘርና በግብአት አቅርቦት ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩንና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማበርከት ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል። ዛሬ ለምረቃ የበቃው ሊቻ የሀድያ ገበሬዎች ሕብረት ሥራ ዩኒየን የወተት ማምረቻ፣ ማቀነባበሪያና ግብይት ማዕከል ከአርሶ አደሩ የሰበሰበውን የወተት ምርት እሴት ጨምሮ ለገበያ እንደሚያቀርብም አስረድተዋል። ዩኒየኑ የራሱን ገቢ ከማሳደግ ባለፈ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን ጠቅሰው፣ የክልሉ መንግስት ጠንካራ የሕብረት ሥራ ማህበራትን ለማጠናከር የጀመረውን ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኡስማን ስሩር በበኩላቸው፥ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ የሆነው የሌማት ትሩፋት ትግበራ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ከጊዜ ወደ እያሳደገው ነው። በክልሉ በግብርናው ዘርፍ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ከቤተሰብ አልፎ በማህበረሰብ ደረጃ ለማረጋገጥ የተጀመረው ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው የገለፁት። ሊቻ የሀድያ ገበሬዎች ሁለገብ ዩኒየን ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ ሽፈራው እንደገለጹት፥ ዩኒየኑ የግብርና ግብዓት አቅርቦትን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች ላይ እየሰራ ይገኛል። ዩኒየኑ 85 ሺህ የሚጠጋ አባላት እንዳሉትና ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገቡን ገልጸው፣ በልማት ስራዎቹም ከአባላቱ በተጨማሪ የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የወተት ማምረቻና ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ከአካባቢው አርሶ አደር ወተት በማሰባሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማህበረሰቡ ያቀርባል ብለዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልሉና የሀድያ ዞን ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የዩኒየኑ አባላት ተገኝተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በምዕራብ ጉጂ ዞን በመኸር እርሻ ከ339 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት ይለማል
May 25, 2026 97
ነጌሌ ቦረና፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፡- በዘንድሮው የመኸር እርሻ የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ከ339 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት ለማልማት ሥራ መጀመሩን የምዕራብ ጉጂ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። ዞኑ በአምስት ዋና ዋና ሰብሎች በሚያከናውነው በዚህ የመኸር አዝመራ ከ8 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ማቀዱን የጽሕፈት ቤቱ የሰብል ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ ታሪኩ ብዙአየሁ ገልጸዋል። በዚህም መሠረት በዘጠኝ ወረዳዎች 339 ሺህ ሔክታር እንደሚለማና በልማት ሥራውም ከ293 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮች እተሳተፉ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። እስካሁን ባለው እንቅስቃሴም በሁሉም የዞኑ ወረዳዎች የመጀመሪያ ዙር የእርሻ ሥራ መጠናቀቁን አረጋግጠዋል። በመኸር አዝመራው በስፋት ስንዴ፣ ጤፍ፣ በቆሎ፣ ቦለቄና ማሾ እንደሚለማ ገልጸው፤ ምርታማነትን ለማሳደግ የተለያዩ ስልቶች ተግባራዊ ይደረጋሉ ብለዋል። ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በበቂ ሁኔታ እንዲቀርብ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው፤ የግብርና ሥራውም በትራክተር፣ በመስመርና በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ እየተካሄደ መሆኑን አስረድተዋል።
የሥራ ገበያ ምኅዳሩን በዲጂታል ሥርዓት በማዘመን ሥራና ሰራተኛ በቀላሉ የሚገናኝበት ዕድል እየተፈጠረ ነው
May 25, 2026 231
አዲስ አበባ፤ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦የሥራ ገበያ ምኅዳሩን በውጤታማ የዲጂታል ሥርዓት በማዘመን ሥራና ሰራተኛ በቀላሉ የሚገናኝበት ዕድል እየተፈጠረ መሆኑን የሥራ ክህሎት ሚኒስትር ሙፈርያት ካሚል ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር ያለማውን ሥራና ሰራተኛ በቀላሉ የሚገናኝበት 'ፈልጉልኝ' የተሰኘ ዘመናዊ የዲጂታል መተግበሪያ ይፋ አድርጓል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈርያት ካሚል በዚሁ ወቅት፤ የዜጎችን የሥራ ዕድል ፈጠራ የሚያዘምኑ የዲጂታል አማራጭ የማሻሻያ እርምጃዎች ተግባራዊ እየተደረጉ ነው ብለዋል። ይፋ የተደረገው 'ፈልጉልኝ' የሥራና ሰራተኛ አገናኝ መተግበሪያም ሥራና ሰራተኛን በቀላሉ የሚያገናኝ የዲጂታል አማራጭ መሆኑን ገልጸዋል። ሥራና ሰራተኛ በዲጂታል ሥርዓት የሚገናኝበት መተግበሪያም በሁሉም ዘርፍ ሙያና ክህሎት ያላቸው ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያሰፋ እንደሆነ ተናግረዋል። መተግበሪያውን ከፋይዳና የኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሰርዓት ጋር በማስተሳሰር በተለያዩ የቋንቋ አማራጮች ተደራሸ የማድረግ ዕድል መፈጠሩን አስረድተዋል። በመተግበሪያው የተካተቱ የተሟላና አስተማማኝ የቴክኖሎጂ አማራጮች ፍትሐዊ የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ምኅዳርን በመፍጠር የማይተካ ሚና እንዳለው አንስተዋል። የሥራ ገበያ ምኅዳሩን በውጤታማ የዲጂታል ሥርዓት በማዘመን ሥራና ሰራተኛ በቀላሉ የሚገናኝበት ዕድል እየተፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ፤ መተግበሪያው በሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ዕውቀት የለማና ደህንነቱ የተጠበቀ ነው ብለዋል። ይህም የመረጃ ሉዓላዊነትና ደህንነትን ለማስጠበቅ ተደማሪ አቅም እንዳለው ገልጸዋል። አምስት የሀገር ዉሰጥ ቋንቋዎችና አጭር የስልክ መልዕክት አማራጭ በመተግበሪያው መካተታቸውም የዜጎች ተጠቃሚነትን ለማላቅ ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይልን በመጠቀም በአፍሪካ ወደ አረንጓዴ ትራንስፖርት ለሚደረገው ሽግግር ግንባር ቀደም ሆና እየሰራች ነው
May 25, 2026 137
አዲስ አበባ፤ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የታዳሽ ኃይል ምንጭ በመጠቀም በአፍሪካ ወደ ንጹህና አረንጓዴ ትራንስፖርት የሚደረገውን ሽግግር በግንባር ቀደምትነት ለመምራት እየሰራች መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያን የትራንስፖርት ዘርፍ ወደ አረንጓዴ፣ዘላቂ እና አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ (ኢ-ሞቢሊቲ) ሥርዓት የሚያሸጋግር ብሄራዊ የኢ-ሞቢሊቲ ስትራቴጂና የትግበራ እቅድ ይፋ ማድረጊያ መርሃግብር እየተካሄደ ይገኛል። በመርሃግብሩ ላይ ከተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች የተወከሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ተወካዮችና የልማት አጋሮች ተገኝተዋል። የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) እንዳሉት፥ አዲሱ ስትራቴጂ የሀገሪቱን የትራንስፖርት ዘርፍ በዘመናዊ መልክ ለመቅረጽ የሚጠቅም ነው ብለዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ ንጹህ ከተሞችን መፍጠር እና የህዝብ ጤናን ማሻሻል፣ ለነዳጅ ግዢ የሚወጣውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ መቆጠብ፣ የሀገሪቱን የኃይል ደህንነት ማረጋገጥ የሚያስችል ምህዳርን መገንባት እንደሚረዳም ተናግረዋል፡፡ ይህ ስትራቴጂ የፖሊሲ እና የህግ ማሻሻያዎችን፣ የኃይል መሙያ ጣቢያዎች ግንባታን፣የህዝብ ትራንስፖርትን በኤሌክትሪክ መተካትን፣ የሀገር ውስጥ ምርትን ማሳደግና የግል ባለሀብቶችን ተሳትፎ ማሳደግን ያካተተ ግልጽ ፍኖተ-ካርታ የያዘ ነው ብለዋል። የኢ-ሞቢሊቲ ሽግግር የአንድ ተቋም ብቻ ኃላፊነት ሳይሆን የጋራ ሀገራዊ ጥረትን የሚጠይቅ መሆኑን ጠቁመው፤ የመንግስት ተቋማትን ጨምሮ የግሉ ዘርፍም ኢንቨስትመንትን እንዲያሳድጉና መሰረተ-ልማቶችን እንዲያስፋፉ ጥሪ አቅርበዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል በበኩላቸው፥ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የትራንስፖርት ወጪንና በነዳጅ ላይ ያለንን ጥገኝነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚቀንሱ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ገበያ የካርቦን ልቀትን መመዝገብ አስገዳጅ እየሆነ በመምጣቱ፣ አረንጓዴ ልማት ለአካባቢ ጥበቃ ብቻ ሳይሆን በገበያ ውስጥ በዘላቂነት ለመቆየት ወሳኝ መስፈርት መሆኑን አብራርተዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የሀገር ውስጥ ምርትና መገጣጠምን በማሳደግ በ2030 የሀገር ውስጥ ምርት ድርሻን ሰላሳ በመቶ ለማድረስ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በቀጣይ የባትሪ ስነ-ምህዳር እና ሰርኩላር ኢኮኖሚ መዘርጋት፣የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቴክኖሎጂ እና ኢንዱስትሪ ፓርኮችን መገንባት፣ ጥራትን ለመጠበቅ አስገዳጅ የሆኑ ብሄራዊ ደረጃዎችን መተግበር እንዲሁም ለባትሪ ምርት ወሳኝ የሆኑትን ማዕድናት ክምችት ጥናት ማፍጠን የትኩረት አቅጣጫዎች ናቸው ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በርካታ ኢንቨስተሮች በኢትዮጵያ ያሉ ማዕድናትን ተጠቅመው በሊቲየም ባትሪ ማምረቻ ዘርፍ ለመሰማራት ፍላጎት እያሳዩ መሆኑን ጠቅሰው፤ የግሉ ዘርፍ በተዘጋጁት ማበረታቻዎችና የቴክኖሎጂ ፓርኮች በመጠቀም በዘርፉ እንዲሰማራ ጥሪ አቅርበዋል። በተጨማሪም ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር በመሆን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ የልህቀት ማዕከላትን ለማቋቋም እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የቴክኖሎጂ፣ ኢኖቬሽንና መሰረተ-ልማት ልማት ዲቪዢን ዳይሬክተር ሮበርት ሊሲንጌ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በዓለም አቀፍና በአፍሪካ ደረጃ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች አጠቃቀም በፍጥነት እያደገ መሆኑንና ኢትዮጵያም በዚህ የሽግግር ሂደት ውስጥ በግንባር ቀደምትነት እየመራች መሆኑን አረጋግጠዋል። ይህ የኢ-ሞቢሊቲ ሽግግር ከልቀት ነፃ የሆኑ ከተሞችን ከመፍጠር ባለፈ፣በነዳጅ ምርቶች ሳቢያ የሚወጣውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ በማስቀረት ለኢኮኖሚው ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የአባል ሀገራትን የኢ-ሞቢሊቲ ጉዞ ለመደገፍ ከአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና ከተባበሩት መንግስታት የአካባቢ ጥበቃ ፕሮግራም ጋር በመሆን የአፍሪካን የኢ-ሞቢሊቲ አህጉራዊ ማዕቀፍ አዘጋጅቶ እንዲፀድቅ ማድረጉን አስታውቀዋል። ይህንን አህጉራዊ ማዕቀፍ ወደ ሀገራዊ ተግባር ለመለወጥ የሚያስችል ፍኖተ-ካርታ መዘጋጀቱንና የ2026 የአፍሪካ ኢኮኖሚ ሪፖርትም የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በምጣኔ ሀብት ሽግግር ላይ ያላቸውን ተፅዕኖ በጥናት መተንተኑን ጠቁመው፣ ኮሚሽኑ የኢትዮጵያን የኢ-ሞቢሊቲ ሽግግር ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን በድጋሚ አረጋግጠዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በክልሉ የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ ነው
May 24, 2026 409
ነገሌ ቦረና፣ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ መሆናቸው ተገለጸ። በምስራቅ ቦረና ዞን ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ የተገነቡ የፊና መስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹን የመረቁት በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በምክትል ርእሰ መስተዳድር ማእረግ የማህበራዊ ዘርፍ ክላስተር አስተባባሪ አቶ ሳዳት ነሻህ ናቸው፡፡ የክልሉ መንግስት የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የቆላማና ዝናብ አጠር አካባቢዎች ዘላቂ ልማት እቅድ በመንደፍ የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቋቋም እየሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብርን የማጠናከር፣ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራና የበጋ መስኖ ልማትን በመተግበር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ መሰራቱን አንስተዋል። በክልሉ የቆላማ አከባቢዎች የአርብቶ አደሩን የመስኖ ልማትን ለማጠናከርና የእንስሳት መጠጥ ወሀ አቅርቦት ችግር ለመፍታት የፊና ፕሮጀክቶችን እውን ለማድረግም ጥረት መደረጉን ገልጸዋል፡፡ በምስራቅ ቦረና ዞን ዛሬ ለምርቃት የበቁት ፕሮጀክቶችም የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ለማሳካትና ለእንስሳት ውሀ አቅርቦት ይውላሉ ብለዋል፡፡ በቀጣይም የክልሉ መንግስት ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ለውጤት በማብቃት የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የሚያደረገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል፡፡ የክልሉ መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ምክትል ሀላፊ ኢንጅነር አለሙ ረጋሳ በምስራቅ ቦረና ዞን የአርብቶ አደሩን የመሰረተ ልማት ተደራሽነት ለማረጋገጥ በግንባታ ላይ ከነበሩ ሶስት የፊና መስኖ ፕሮጀክቶች መካከል ሁለቱ ለአገልግሎት መብቃታቸውን ጠቁመዋል። በዞኑ ሊበንና ጎሮ ዶላ ወረዳ በግንባታ ላይ ከነበሩት ሁለቱ ሙሉ በሙሉ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹም በቆላማና ዝናብ አጠር አከባቢዎች የሚታየውን የድርቅ ተጋላጭነት በዘላቂነት ለመቋቋም፣ ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማትና ለእንስሳት መጠጥ ውሀ አቅርቦት እንዲሁም ለመኖ ልማት እንደሚውሉ አመላክተዋል። የክልሉ መንግስት ግንባታቸው ለተጠናቀቁት የፊና መስኖ ፕሮጀክቶች 518 ሚሊዮን ብር ወጭ ማድረጉን አስታውቀዋል፡፡ የመስኖ ፕሮጀክቶቹ 8 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሜትር ኪውብ የዝናብ ውሀ የመያዝ አቅም ያላቸው እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡ የምስራቅ ቦረና ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱረዛቅ ሁሴን በበኩላቸው ፕሮጀክቶቹ ከ465 ሄክታር በላይ መሬት በመስኖ የማልማት አቅም አላቸው ብለዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹ አርብቶ አደሩን በመስኖ ልማት በመሰማራት ተጠቃሚ ከማድረግ ባሻገር ከቀየው ሳይርቅ ለእንስሳቱ የመጠጥ ውሀ እንዲያገኝ የሚያስችሉት መሆኑን አመልክተዋል። በዞኑ የሊበን ወረዳ ነዋሪ አቶ ቃሲም ገመዳ በበኩላቸው የፕሮጀክቶቹ መገንባት የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጥያቄዎች የመለሱ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ በአካባቢው የተሰሩት የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች ቀደም ሲል ለእንስሳት መኖና የመጠጥ ውሀ ፍለጋ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ እንደሚያስቀሩላቸው ተናግረዋል።
በክልሉ በፍራፍሬና በቡና ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል − ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
May 24, 2026 338
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ) ፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በፍራፍሬ እና በቡና ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ በክልሉ በፍራፍሬ፣ በቡናና ሥራስር ተክሎች ልማት ለሀገር ውስጥ እና ለውጪ ገበያ ለማቅረብ የተከናወኑ ሥራዎች ውጤት ተገኝቶባቸዋል። በዚህም ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑና ለውጪ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶች ላይ ይበልጥ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በበጋ መስኖና በመኸር እርሻ ከ107 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በፍራፍሬና በአትክልት መሸፈኑን ተናግረዋል። በዋናነትም ሙዝ፣ ማንጎ፣ አቮካዶ እና የደጋ ፍራፍሬ እንዲሁም የተለያዩ የጓሮ አትክልቶች መልማታቸውን ርዕሰ መስተዳድሩ ጠቁመዋል። ከሀገራዊ ለውጡ በፊት በክልሉ ከ60 ሺህ ሄክታር ያልበለጠ የሙዝ ማሳ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ጥላሁን፣ በአሁኑ ወቅት በአራት እጥፍ አድጎ ከ240 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት መልማቱን ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር ለፍራፍሬ ልማት ሽፋን እያደገ መምጣት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም ገልጸዋል። እንደ አቶ ጥላሁን ገለጻ በተያዘው ዓመት በፍራፍሬ የሚለማውን መሬት ሽፋን ለማሳደግ በተያዘ ዕቅድ በተለያዩ አካባቢዎች የሚተከሉ ከ25 ሚሊዮን በላይ የአቮካዶ፣ ማንጎ እና አፕል ችግኞች ተዘጋጅተዋል። በማህበር የተደራጁ ወጣቶችም በፍራፍሬ ልማት፣ በግብይትና ማቀነባበር የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸው ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ነው የገለጹት። የቡና ልማትን ከማስፋፋት አንጻር ለቡና ምቹ በሆኑ ሁሉም የክልሉ አካባቢዎች ልማቱ እየተከናወነ መሆኑን ያመለከቱት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በጌዴኦ ዞን ቡናን ስፔሻላይዝድ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። የቡና ልማቱን በጥምር ግብርና በማከናወን የአርሶ አደሩን ዘርፈ ብዙ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራትም ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። በክልሉ የቡና ልማቱን ለማስፋት በተያዘው ዕቅድ መሰረት ዘንድሮ ከተዘጋጁ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና ችግኞች አብዛኞቹ ባለፈው ሚያዝያ ወር መተከላቸውን ገልጸው፣ ቀሪዎቹ በቀጣይ ሐምሌ ወር ይተከላሉ ብለዋል።
በአማራ ክልል የግብርናውን ክፍለ ኢኮኖሚ የሚያጠናክሩ ተግባራት ትኩረት የተሰጣቸው ናቸው- ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
May 24, 2026 258
ጎንደር ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የግብርናውን ክፍለ ኢኮኖሚ የሚያጠናክሩ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ አስታወቁ ። የጎንደር የተቀናጀ አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ የግንባታ ማስጀመሪያ ስነ ስርዓት በጎንደር ዙሪያ ወረዳ ዛሬ ተካሂዷል ። ርእሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንደገለጹት በክልሉ የግብርናውን ዘርፍ ኢኮኖሚያዊ እድገት የሚያጠናክሩና የሚያሳልጡ ተግባራት ትኩረት የተሰጣቸው ናቸው ። በክልሉ ግንባታው የተጀመረው የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ የዚሁ አካል መሆኑን ጠቁመው ፓርኩ በክልሉ ዋነኛ የኢኮኖሚ ማእከል እንደሚሆንም አመልክተዋል ። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በበኩላቸው በሀገሪቱ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ የሚደረገውን መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር በማፋጠን ረገድ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ወሳኝ የእድገት ምሰሶዎች ናቸው ብለዋል። የተቀናጀ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የግብርና ምርት እሴት ጨምሮ ለሀገርና ለውጪ ገበያ ለማቅረብ ምቹ የኢኮኖሚ መሠረት የሚጥሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። ዛሬ ግንባታው የተጀመረው አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ የአካባቢውን የግብርና ምርት በስፋት በመጠቀም ለአካባቢው አምራች አርሶ አደሮች ሰፊ የገበያ እድል የሚፈጥር እንደሆነም አመልክተዋል። ፓርኩን በሂደት ወደ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን በማሳደግ እንደ ሀገር ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ የሚደረገውን ሽግግር ለማሳለጥ ምቹ መደላድል የሚፈጥር መሆኑን ጠቅሰዋል። ፓርኩ ለግብርና ምርቶች የገበያ እድል በማመቻቸት ለወጣቶች ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር እንዲሁም ለከተሞች ገቢ ማደግና ለቴክኖሎጂ ሽግግር የላቀ አስተዋጽኦ እንዳለውም ጠቁመዋል። የአማራ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ብርሀኑ ጣምያለው ኢንዱስትሪ ፓርኩ በ256 ሄክታር መሬት ላይ ግንባታው እንደሚካሄድ ገልጸዋል። የፓርኩ ግንባታ ከ8 ቢሊዮን ብር በላይ የኢንቨስትመንት ወጪ እንደሚጠይቅ ጠቁመው ስራ ሲጀምር ለ55 ሺህ ወገኖች ቋሚ እንዲሁም ከ200ሺህ በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎች ጊዚያዊ የስራ እድል ይፈጥራል ብለዋል። ፓርኩ በአመት ከአንድ ሚሊዮን ቶን በላይ ምርት የማቀናበር አቅም ሲኖረው እሴት የተጨመረባቸውን ምርቶች ለውጪ ገበያ በማቅረብ የውጪ ምንዛሪ የሚያስገኝ መሆኑንም አስታውቀዋል። የማእከላዊ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አወቀ አስፈሬ ዞኑ ለአግሮ ኢንዱስሪዎች ግብአት የሚውል ሰሊጥ፣ አኩሪ አተርና ጥጥ የመሳሰሉ የግብርና ምርቶች በስፋት የሚመረቱበት እንደሆነ ተናግረዋል ። ኢንዱስትሪ ፓርኩ ለአካባቢው የኢኮኖሚ መነቃቃት አስተዋፅኦው የላቀ መሆኑንም አመልክተዋል። በኢንዱስትሪ ፓርኩ የግንባታ ማስጀመሪያ ስነ ስርአት ላይ የፌደራል፣ የክልል እንዲሁም የጎንደር ከተማና የማእከላዊ ጎንደር ዞን አመራሮችና የአካባቢው ማህበረሰብ ተገኝተዋል።
በሐረሪ ክልል አቮካዶን በተሻለ ደረጃ በማምረት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማጎልበት ወደ ስራ ተገብቷል
May 24, 2026 241
ሐረር፣ ግንቦት 16/2018(ኢዜአ):- በሐረሪ ክልል የአቮካዶ ልማትን በተሻለ ደረጃ በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማጎልበት ወደ ስራ መገባቱን የክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ አስታወቀ። በኢትዮጵያ ከፍተኛ የገበያ ተፈላጊነት ያላቸውንና አምራች አርሶ አደሮችን በአጭር ጊዜ ተጠቃሚ የሚያደርጉ እንደ አቮካዶ ያሉ ከፍተኛ እሴት ያላቸው አትክልትና ፍራፍሬ ልማቶች በስፋት እየተስፋፉ ይገኛሉ። የሐረሪ ክልልም ያለውን የተወሰነ የእርሻ መሬት በቴክኖሎጂ በማገዝ ምርታማነትን ለመጨመርና የአካባቢውን ማህበረሰብ የውስጥ ፍጆታ ከመሸፈን ባለፈ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ያቀደውን ስራ ስኬታማ ለማድረግ፣ የአመራሩና የባለሙያው አቅም መገንባት ወሳኝ መሆኑ ይገለጻል። በክልሉ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ለማስጀመር በልማቱ ዙሪያ ለዘርፉ አመራሮች፣ ባለሙያዎችና ባለድርሻ አካላት ስልጠና በመሰጠት ላይ ይገኛል። በመድረኩ የተገኙት የክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ነስረዲን አህመድ ለኢዜአ እንዳሉት በክልሉ ከአረንጓዴ አሻራ ልማት ጋር በማያያዝ አቮካዶን የማልማት ስራ እየተከናወነ ነው። ይህንን ተግባር ለማጎልበት በክልሉ በብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም የተለያዩ ስራዎች ተቀርጸው ተግባራዊ የማድረግ ስራ መጀመሩን ተናግረዋል። በዚህም የአቮካዶ ልማት የሚከናወንበት ቦታን የመለየት ስራ መከናወኑን የተናገሩት አቶ ነስረዲን በክልሉ በአራቱ የገጠርና ከተማ ወረዳዎች ውስጥ ተግባራዊ እንደሚደረግ ተናግረዋል። በተለይም የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ የአቮካዶ ልማት የዝግጅት ስራዎች አንዱ መሆኑን ጠቁመው ችግኝ የማፍላትና የማዳቀል እንዲሁም የአርሶ አደሮችን ግንዛቤ የማሳደግ ስራዎች መከናወናቸውን አብራርተዋል። ይህ የአቮካዶ ልማት ኢንሼቲቭ በቴክኖሎጂ በማዘመን አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ማድረግ፣ ምርቱን ለዓለም አቀፍ ገበያ በማቅረብ የውጭ ምንዛሬን ማሳደግ እንዲሁም በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እገዛ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። የሐረሪ ክልል አየር ፀባይ ለአቮካዶ ልማት ምቹ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ መሐመድ ሬድዋን ናቸው። ይህ ፕሮግራም በክልሉ ምርትና ምርታማነትን በማጎልበት የአርሶ አደሩን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ሥራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር ትልቅ እገዛ ከማድረጉ ባለፈ ለወጣቶችም የስራ እድል ይፈጥራል ብለዋል።
በዲላ ከተማ የተዘጋጀው "ቡኖ - ማላ" ኤክስፖ ምርቶችንና የኢንቨስትመንት እድሎችን ለማስተዋወቅ አስችሏል
May 24, 2026 151
ዲላ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፡-ከ40 በላይ የንግድ ተቋማትና አጋር አካላት ተሳትፈውበት በዲላ ከተማ የተዘጋጀው "ቡኖ - ማላ" ኤክስፖ ምርቶችን እና የኢንቨስትመንት እድሎችን ጭምር ለማስተዋወቅ መልካም እድል መሆኑ ተገለጸ። ለሁለት ተከታታይ ቀናት የሚካሄደውን "ቡኖ - ማላ" ዓለም አቀፍ ኤክስፖ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት የልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ኢንጂነር ስለሺ ኮሬ (ዶ/ር) በይፋ ከፍተውታል። በዚሁ ጊዜ ባስተላለፉት መልዕክትም በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም በቁም እንስሳት ሃብት የሚታወቀው የጌዴኦ ዞን ምርታማነቱ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በቡና እና ሌሎችም የልማት መስኮች የተሰማሩ ከ40 በላይ የንግድ ተቋማትና አጋር አካላት የተሳተፉበት ዓለም አቀፍ ኤክስፖ መሆኑ ትልቅ ትርጉም አለው ብለዋል። በመሆኑም ኤክስፖው ምርትና አገልግሎትን እንዲሁም የኢንቨስትመንት እድሎችን ጭምር ለማስተዋወቅ መልካም ዕድል መሆኑን ተናግረዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡናና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አማኑኤል ብሩ፤ በክልሉ የይርጋጨፌ፣ የኮቾሬና አማሮን ጨምሮ ሌሎችም አካባቢዎች የባለ ልዩ ጣዕም ቡና የሚመረትባቸው መሆናቸውን አንስተዋል። ቡናን በጥሬ ከመላክ ባለፈ በልዩ ጣዕሞች አዘጋጅቶ እሴት ጨምሮ በመላክ መልካም ጅምሮች መኖራቸውን አንስተው፣ ኤክስፖው ጥሩ ተሞክሮ ለመቀመርና ምርቶችን ለማስተዋወቅ የጎላ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በዞኑ በግብርና ልማት በተለይም በቡና፣ እንሰትና የቁም እንስሳት ሃብት እምቅ አቅም መኖሩን አንስተው ኤክስፖው ይህንኑ ይበልጥ ለማስተዋወቅ መልካም ዕድል ነው ብለዋል። የጌዴኦ ዞን የባህላዊ መልከዓ ምድር ማዕከል መሆኑን አንስተው በሆቴልና ቱሪዝም ዘርፍ ለሚሰማሩ አካላት አዋጭ የገበያ ዕድል እንዳለም ተናግረዋል። በዞኑ ከ80 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቡና የተሸፈነ መሆኑን የገለጹት ዋና አስተዳዳሪው፣ የተለያየ ደረጃ ያላቸው የቡና ምርቶችንም ወደተለያዩ የወጭ ሀገራት እንደሚላኩ ተናግረዋል። የይርጋጨፌ ቡና ገበሬዎች ሕብረት ሥራ ዩኒየን ተወካይ ቤተልሔም ዳንኤል፤ ዩኒየኑ ጥራቱን የጠበቀ ጥሬ ቡና ለውጭ ገበያ ከማቅረብ ባለፈ የውጭ ገዥዎችን መሰረት ያደረገ እሴት የተጨመረበት ቡና ለገበያ እያቀረበ መሆኑ አንስተዋል። በተለይ በቀን ከዘጠኝ ኩንታል በላይ በራሱ ልዩ ጣዕም ተቆልቶና ተፈጭቶ የተዘጋጀ ቡና ለገበያ በማቅረብ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን አንስተው፣ በኤክስፖውም ተጨማሪ የገበያ ትስስር እየፈጠሩ መሆኑን ተናግረዋል። በቡና ንግድ በእሴት ሰንሰለቱ ያሉ ተዋንያንን መቀነስ ለትርፋማነት መሰረት መሆኑን ያነሱት ደግሞ ወልትአብንዶ የቡና አቅራቢ ማህበር ሰብሳቢ ወይዘሮ ሽታዬ ሃጥያ ናቸው።
በኦሮሚያ ክልል የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ለማቀላጠፍ የአሰራር ማሻሻያና ለተቋማት ግንባታ ትኩረት ተሰጥቷል
May 24, 2026 155
አዳማ፤ግንቦት 16/2018(ኢዜአ)፦በክልሉ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ለማቀላጠፍ ለአሰራር ማሻሻያና ለተቋማት ግንባታ ትኩረት መሰጠቱን በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ ገለፁ። በክልሉ ምስራቅ ሸዋ ዞን በቴክኖሎጂ የተደራጀ የአስተዳደር ህንፃ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ በወቅቱ እንደገለፁት፥ የክልሉ መንግሥት የአገልግሎት አሰጣጥ ለማቀላጠፍ የአሰራር ማሻሻያና በተቋማት ግንባታ ላይ በትኩረት እየሰራ ነው። የህዝቡን የልማት ጥያቄዎችና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በቅርበት ለመፍታት የቀበሌ አደረጃጀትን በቅርበት በመዘርጋት የአገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን ላይ መሰራቱን አስታውሰዋል። ይህም ህዝቡ አገልግሎቱን በቅርበት በማግኘት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማቱን እንዲያፋጥን ከማስቻሉም በላይ የመልካም አስተዳደር ቅሬታዎችን መፍታት መቻሉን አመልክተዋል። የተገልጋይን እርካታ ለማሳደግም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነት ላይም በስፋት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስም ባለፉት አምስት ዓመታት ከተሰሩት ከ90ሺህ በላይ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሰረተ ልማቶች ውስጥ 70 በመቶ የሚሆኑት በህዝብ ተሳትፎ መሰራታቸውን ተናግረዋል። የምስራቅ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባቡ ዋቆ በበኩላቸው፥ ዞኑ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ለማቀላጠፍ ሴክተር መስሪያ ቤቶችን ወደ አንድ ማእከል የማምጣትና በቴክኖሎጂ የማደረጀት ተግባር ማከናወኑን አንስተዋል። የዚሁ አካል የሆነው አዲሱ የዞኑ አስተዳደር ህንፃም ለተገልጋዮች ምቹ ከመሆኑ ባለፈ አስተዳደሩ ያወጣ የነበረን ኪራይ መቅረፍ እንደሚያስችል ጠቁመዋል። ይህም 17 መስሪያ ቤቶችን በአንድ ላይ የያዘ ከመሆኑም ባለፈ ከወረዳዎች ጋር በቴክኖሎጂ የተያያዘ መሆኑን ተናግረዋል። ህንፃው ቤተ መጻሐፍት፣ የመሰብሰቢያ አዳራሾች፣ የህፃናት ማቆያ፣ የተሽከርካሪ ማቆሚያና ሌሎችን የያዘና በዲጂታል ቴክኖሎጂ የተደራጀ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። በዚህም የዲጂታል አገልግሎት ለማቀላጠፍ የሚያስችል ምቹ የመስሪያ ቦታ መገንባቱን ገልጸዋል። በምረቃው ፕሮግራም ላይ የፌዴራልና የክልሉ መንግሥት የስራ ሃላፊዎች፣ አባገዳዎችና ሃደ ሲንቄዎች እንዲሁም ከዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የተውጣጡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን የሚወስን ቁልፍ የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ ነው
May 23, 2026 598
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት የሀገርን ኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን የሚወስን ቁልፍ የብሔራዊ ጥቅምና የሕልውና ጉዳይ መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ገለጹ። ጥያቄው ታሪካዊነትን ከመልክዓ-ምድራዊነት፣ ሕጋዊነትን ደግሞ ከፍትሐዊ ተጠቃሚነት ጋር ያሰናሰለ ጠንካራና ምክንያታዊ መሠረት ያለው መሆኑን አስገንዝበዋል። ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያና የቀይ ባሕር ዳርቻ ትስስር በሀገረ-መንግሥት ምሥረታና ግንባታ ታሪክ ውስጥ እጅግ የጠበቀ ነው ብለዋል፡፡ ለአብነትም በአክሱም ሥልጣኔ ዘመን የነበረው ኃያልነትና በአዱሊስ ወደብ አማካኝነት ከመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ጋር የተደረገው ሰፊ የንግድ ልውውጥ ከቀይ ባሕር ቁርኝት የመነጨ እንደነበር አብራርተዋል። በታሪክ ሂደት ውስጥ ኢትዮጵያን ከቀይ ባሕር ለማራቅ የውስጥ ባንዳዎችን በማሰለፍ ጭምር የሸረቡት ሴራና የተሳሳተ ስሌት በእጅጉ የሚያስቆጭ የታሪክ ስብራት መሆኑን ጠቁመዋል። ዛሬም ቢሆን የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለማደናቀፍ የውጭ ኃይሎችና የእነርሱ ተላላኪ የሆኑ የሀገር ውስጥ ኃይሎች በተሳሳተ ስሌት እየተጓዙ መሆኑን አክለዋል። ባለፉት ሦስት አስርት ዓመታት የባሕር በር ጉዳይን ማንሳት እንደ ተንኳሽነት የሚቆጠርበትን አደገኛ ትርክት በመስበር፣ ወሳኝ የምክክርና የንግግር አውድ እንዲፈጠር መደረጉን ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ይፋ ካደርጉበት ጊዜ ጀምሮም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በህዝብ ለህዝብ ግንኙነትና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ሥራዎች ማከናወኑን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያውያን በብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ ላይ የተደመረ ዕይታና ፅኑ አቋም ሊኖራቸው ይገባል ብለዋል። በምንም ዓይነት የፖለቲካ ልዩነት የትውልድን ጥያቄ አሳልፎ መስጠት እንደማይገባና ለብሔራዊ ጥቅምና ፍላጎት መከበር በትብብር መቆም እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የባሕር በር ፍላጎቷን በሰላማዊና በሰጥቶ መቀበል መርህ እያቀረበች መሆኑን በመጥቀስ፤ በዓለም አቀፍ ደረጃ የላቲን አሜሪካ ሀገራት ቦሊቪያና ፔሩ፣ ብራዚልና ፓራጓይ፤ በአፍሪካ የማሊ፣ ሴኔጋልና ኮትዲቯር የተጠቀሙባቸውን የጋራ መፍትሔዎች በተሞክሮነት አስረድተዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 መሠረት የኢኮኖሚ ውህደት የሰፈነባት አህጉር ለመፍጠር በቀጣናው ሀገሮች መካከል የኃይል ትስስር በመፍጠር የባሕር በር ፍላጎቷን በሰፊው እያስረዳች መሆኑንም ገልጸዋል። የባሕር በር አለመኖር በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ጫና እያሳደረ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፤ በየዓመቱም ኢትዮጵያ ለወደብና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ብቻ ከአንድ ነጥብ አምስት እስከ ሁለት ቢሊዮን ዶላር ወጪ ለማድረግ መገደዷን ተናግረዋል። ይህም በወጪና ገቢ ንግድ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት እንዲሁም በጠቅላላው የዕድገት ጉዞ ላይ ትልቅ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩን አስገንዝበዋል። በመሆኑም መገናኛ ብዙኃን ብሔራዊ መግባባትን በማጉላት፤ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ማስረዳት እንዳለባቸው ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ የኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነትን በማስከበር ዕድገትና ብልፅግና ከሚወስኑ ቁልፍ ብሔራዊ ጥቅም ጉዳዮች ውስጥ አንዱ ነው ብለዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የተገነባውን የተቀናጀ የከተማ ግብርና ማዕከል መረቁ
May 23, 2026 363
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የሚገኘውን የተቀናጀ የከተማ ግብርና ማዕከል መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በመልዕክታቸው፤ የተቀናጀ የከተማ የግብርና ማዕከሉ በ3 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ እና 18 ሱቆችን እንዲሁም 18 ሼዶችን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። አዲስ አበባ ለሁሉም የምትመች የጋራ ቤትና ልማቷም አካታች መሆኑን አመልክተዋል። ባለፈው ሥርዓት አርሶ አደሩ የሚገፋበት፣ መሬቱ ብቻ ተፈልጎ እርሱ የሚዘነጋበት የነበረ በመሆኑ ለለውጡ መምጣት ገፊ ምክንያት እንደነበር አስታውሰዋል። የአሁኑ የከተማ አስተዳደር አርሶ አደሩን በሁሉም የከተማ ልማት ውስጥ አካቶ አብሮ እንዲለማ እና ተጠቃሚነቱ እንዲረጋገጥ እያደረገ መሆኑን ከንቲባ አዳነች ገልጸዋል። አርሶ አደሩ ለልማት በሚነሳበት ወቅት ተገቢውን ካሳ ከማግኘት ባለፈ ከልማቱ ቀጥተኛ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደም በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ በ14 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተገነባው የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ልህቀት ማዕከል እና ዛሬ በለሚ ኩራ የተመረቀው ማዕከል የዚሁ ማሳያ መሆናቸውንም ነው ያብራሩት። እነዚህን መሰል ማዕከላት የከተማው ነዋሪ የሚያጋጥመውን የዋጋ ንረት ለመከላከል እና በተመጣጣኝ ዋጋ የግብርና ምርቶችን ለማቅረብ ያስችላሉ ያሉት ከንቲባዋ፣ አሰራሩ በጋራ ማደግንና ተባብሮ መበልጸግን የሚያሳድግ መሆኑን ገልጸዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ይህንን ግዙፍ ስራ በማቀድ፣ በማስተባበርና ውጤታማ እንዲሆን በማድረግ ረገድ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
በካፋ ዞን የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት አሳድገዋል
May 23, 2026 225
ቦንጋ ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦በካፋ ዞን ህብረተሰቡን በማሳተፍ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማሳደጋቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ፡፡ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በካፋ ዞን ሺሾእንዴ ወረዳ ከ44 ሚሊዮን ብር በላይ በሚሆን ወጪ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል። ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል ሞዴል ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት፣ የወሺ ፏፏቴ የቱሪስት መዳረሻ፣ ሞዴል ጤና ኬላ እንዲሁም የኖባ ሽመሮ እና ወሺ ጊዳ የመንገድ መሰረተ ልማት ይጠቀሳሉ። የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ እንደገለፁት፤ በዞኑ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት አሳድገዋል። ዛሬ የተመረቁ የተለያዩ ፕሮጀክቶችም የዚሁ ማሳያዎች ናቸው ያሉት አቶ እንዳሻው፣ በዞኑ በዚህ ዓመት ህብረተሰቡን በማሳተፍ የመሰረተ ልማት ችግሮችን ለመቅረፍ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በትምህርቱ ዘርፍ የሚስተዋለውን የጥራትና ውጤታማነት ችግር ለመፍታትም ሞዴል ቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። የጤና አገልግሎቶችን ተደራሽ ማድረግ ትኩረት የተሰጠው አንዱ ተግባር ነው ያሉት አስተዳዳሪው በዚህም የጤና ተቋማትን ከመገንባት ባለፈ አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የተሰራው ስራ ውጤት ማስመዝገቡን ነው የተናገሩት፡፡ የቱሪስት መዳረሻን በማልማት ረገድ ለወጣቶች ስራ ዕድል በመፍጠርና ቱሪስቶችን ለመሳብ በተደረገው ጥረት ዛሬ የተመረቀው የወሺ ፏፏቴ መዳረሻም የተደበቀውን እምቅ ሀብት አጉልቶ ያወጣ ነው ብለዋል። የሺሾእንዴ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ደምሴ ገብረማርያም በበኩላቸው፣ በወረዳው የህብረተሰቡ የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለሆኑ የመንገድ፣ የትምህርት፣ የጤናና ሌሎች መሰረተ ልማት ምላሽ ለመስጠት እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። በዛሬው እለት የተመረቁት መንገዶች አርሶ አደሩ ምርቱን ለገበያ እንዲያወጣ እንዲሁም በፍጥነት የጤና አገልግሎትን እንዲያገኝ ትልቅ አስተዋጽኦ ያለው ነው ብለዋል፡፡ የወረዳው ነዋሪዎችም ከዚህ ቀደም በአካባቢያቸው መንገድ ባለመኖሩ ምርታቸውን ወደ ገበያ ለማውጣትም ሆነ ወደ ጤና ተቋማት ፈጥኖ ለመድረስ ይቸገሩ እንደነበር ተናግረዋል። ዛሬ የተመረቁት የትምህርት፣ የመንገድና የጤና ተቋማት ለበርካታ ዓመታት ይነሱ የነበሩ ጥያቄዎችን የመለሱ መሆናቸውን አስረድተዋል።
በኦሮሚያ ክልል በለውጡ አመታት በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ከ43ሺህ በላይ ደርሰዋል -ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ
May 23, 2026 360
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ከለውጡ በፊት ከ10ሺህ በታች የነበረው የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች በለውጡ አመታት በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ከ43ሺህ በላይ መድረሳቸውን የክልሉ ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በሞጆ ከተማ የተገነባውን የግራንዴር ሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካን መርቀዋል። የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት የኦሮሚያ ክልልን የኢንቨስትመንት ማዕከል ለማድረግና የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሞተር እንዲሆን በትኩረት እየተሠራ ይገኛል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት የመደመር እሳቤን መሠረት በማድረግ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት ሰፊ ሥራ መሠራቱንም ገልጸዋል። በክልሉ ቡልቡላ እና ግንባታው በመጠናቀቅ ላይ የሚገኘው የነቀምቴ ኢንዱስትሪ ፓርኮችን እንዲሁም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ግንባታው የተጀመረውን ገዳ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን በዋቢነት አንስተዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በገዳ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ብቻ በአሁኑ ወቅት ከ70 በላይ ባለሃብቶች ወደ ኢንቨስትመንት ለመግባት በሂደት ላይ እንደሚገኙ እና ከ30 በላይ የሚሆኑት ደግሞ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ ደርሰዋል ብለዋል። የክልሉ መንግሥት ቢሮክራሲን በመቀነስ፣ አሠራሮችን በማሳለጥ፣ መሠረተ ልማቶችን በማሟላት እና ወጣቶች ክህሎት ይዘው የልማቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ በማድረግ ምቹ የኢንቨስትመንት ከባቢን እየፈጠረ መሆኑንም አስታውቀዋል። የዛሬው የግራንዴር ሴራሚክ ፋብሪካ ምረቃም የዚሁ እንቅስቃሴ ውጤት አካል መሆኑን ነው የገለጹት። የግብርናው ዘርፍም ከተለመደው አሠራር ወጥቶ ወደ ኢንቨስትመንት እየተሸጋገረ መሆኑን ጠቁመው፣ በተያዘው መንገድ በቁርጠኝነት ከተሠራ የክልሉም ሆነ የሀገሪቱ ብልጽግና በአጭር ጊዜ እውን እንደሚሆን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው፤ ለቀጣናዊ ትስስር እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት የላቀ ሚና አለው
May 23, 2026 224
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው፤ ለቀጣናዊ ትስስር እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት የላቀ ሚና እንዳለው የዘርፉ ምሁራን አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ቀደም ሲል፤ የቀይ ባህር ጉዳይ ለኢትዮጵያ ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ መልክዓ ምድራዊ (ጂኦግራፊያዊ) እና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄ መሆኑን መግለጻቸው ይታወሳል። ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችበት መንገድ ሕጋዊና ተቋማዊ መሰረት እንደሌሎው የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ኢትዮጵያና ቀይ ባህር ለዘለዓለም ተነጣጥለው ሊኖሩ እንደማይችሉና ጥያቄው በፍትሐዊ፣ በሰላማዊ፣ በሰጥቶ መቀበል መርህ ምላሽ እንዲያገኝ የሚደረገው ጥረት እንደሚቀጥል ማስታወቃቸው ይታወሳል። የኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የአመራርና አስተዳደር ኮሌጅ ምክትል ዲን መሀመድ አሊ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድና በቀጣናው ላይ ከፍተኛ የሰላም ማስከበር ሚና ስትጫወት የቆየችና አሁንም ይህንኑ እያደረገች ያለች ሀገር መሆኗን ገልጸዋል። በተለይም በሰላም ማስከበር የሰለጠነ የሰው ኃይል በማሰማራት፣ መስዋዕትነት ጭምር እየከፈለች የአካባቢውን ሰላምና ጸጥታ በማስከበር በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተች መሆኗን አብራርተዋል። ይህ የሰላም ማስከበር ልምዷ በቀይ ባህር ቀጣና ላይ ካላት ስትራቴጂካዊ ጥቅም ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት እንዳለውም ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ አጠቃላይ የወጪና ገቢ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መሰረት ያደረገው ቀይ ባህርን መሆኑን አመልክተው፤ በዚሁ ቀጣና ሀገሪቱ የተለየ ፍላጎትና ጥቅም ሊኖራት እንደሚገባ አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ወደ ባህር በር መመለስ ለጎረቤት ሀገሮችም ጭምር የጋራ ጥቅም እንዳለው የቀጣናው ሕዝቦች እንዲገነዘቡ ማድረግ ያስፈልጋል ያሉት ምሁሩ፤ አካባቢው ላይ አስተማማኝ ሰላምና ጸጥታ እንዲሰፍን ኢትዮጵያ ትልቁን ሚና እንደምትጫወት ተናግረዋል። ይህም ጠቃሚነቱ ለአንድ ሀገር ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ጎረቤት ሀገሮች እንደሚሆን ማሰብ ይገባል ብለዋል። በቀጣናው የሚኖረው ማህበረሰብ በቋንቋ፣ በእምነት፣ በባህልና በኢኮኖሚ በከፍተኛ ደረጃ የተሳሰረ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህንን ቀጣናዊ ትስስር አጠናክሮ የመቀጠል ጥቅም አጠቃላይ የቀጣናው ሕዝብ እንዲገነዘበው የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን በማጠናከር በኩል በትኩረት መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ የዓለም አቀፍ ግንኙነት ረዳት ፕሮፌሰር ናርዶስ ሃዋዝ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የቀይ ባህር ጉዳይ ሁል ጊዜም ቢሆን የታሪካዊ ባለቤትነት ጥያቄን አብሮ የሚያስነሳ መሆኑን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነትን ለማረጋገጥ የምታደርገው ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ትልቁ ሚናውና ማጠንጠኛው ከዚሁ ታሪካዊ እውነታ ጋር የተያያዘ መሆኑን ገልጸዋል። በመንግሥታት ደረጃ የሚደረገው ዲፕሎማሲያዊ ንግግርና ውይይት እንደተጠበቀ ሆኖ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ድንበር ተሻጋሪ የሆኑ የሕዝቦች የጋራ ማንነት၊ ባህልና ታሪክ መኖሩንና በእነዚህ ሕዝቦች መካከል ባለው ትስስር ላይ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን በማጠናከር መቀራረብን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚገባ ተናግረዋል። ይህ የሕዝብ ለሕዝብ ትስስር ደግሞ ውሎ አድሮ ቀጣናውን በራሱ ጊዜ ወደ አንድ የተዋሃደ ማህበረሰብ ሊመራው እንደሚችልም አመልክተዋል።
የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ ለፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት ተገንብቷል
May 23, 2026 119
ሃዋሳ፤ ግንቦት 15/2028 (ኢዜአ)፡- የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ ለፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት መገንባት መቻሉን የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሃመድ ገለጹ፡፡ የመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽን ለመከላከያ ሰራዊት አባላትና ለቋሚ ሲቪል ሰራተኞቹ በሃዋሳ ያስገነባቸውን 232 የጋራ መኖሪያ ቤቶች በእጣ የማስተላለፍ መርሃ ግብር አከናውኗል፡፡ በወቅቱም ሚኒስትሯ አይሻ መሃመድ (ኢ/ር) እንደገለጹት፤ የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ በፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት መገንባት ተችሏል። የለውጡ መንግስት እውን ባደረገው የሪፎርም ስራ መሰረት በወጣው የመከላከያ ሰራዊት አዋጅ የሰራዊቱን ክብር የሚመጥኑ ጥቅማ ጥቅሞች በሚገባ እንዲከበሩ ተደርጓል ብለዋል። በዚህም ለሀገር ሉዓላዊነትና ለህዝብ ሰላም የህይወት መስዋዕትነት ለሚከፍል የመከላከያ ሰራዊት ጥቅም መከበር የሚደረግ ድጋፍ ውለታ ሳይሆን የክብር ግዴታ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽን የተገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች መንግስትና ህዝብ ለሰራዊቱ ያላቸውን ምስጋናና ፍቅር በተግባር ያሳዩበትና ሀገራዊ ህሊና የወለዳቸው የእውቅና ውጤቶች ናቸው ሲሉ ገልጸዋል፡፡ ፕሮጀክቱ በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ የተደረገው የጋራ ርብርብ የኢትዮጵያውያንን የመደጋገፍና የአብሮነት ጥበብ ያሳየ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሯ የመኖሪያ ቤቶቹ ፋውንዴሽኑ በራሱ ባለሙያዎች የገነባው መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ የጋራ መኖሪያ ቤቶቹ ግንባታ ሰራዊቱ ራሱንና ቤተሰቡን በተረጋጋ መንገድ በማኖር ሀገራዊ ግዳጁን በተገቢው እንዲወጣ የሚያደርግና ለሃዋሳ ከተማ ተጨማሪ ውበትና የልማት ውጤት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የሲዳማ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ሃላፊ አቶ በየነ በራሳ በበኩላቸው የመከላከያ ሰራዊት ለሀገር ሉአላዊነት፣ ክብርና ለህዝብ ሰላም በታማኝነት የሚያገለግልና የህይወት መስዋዕትነት የሚከፍል ነው ብለዋል፡፡ በዛሬው እለት የተመረቁ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ከ820 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የመከላከያ ሚኒስቴር ፋውንዴሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ሜጀር ጄኔራል ደረጀ መገርሳ ናቸው፡፡ የጋራ መኖሪያ ቤቶቹ በአነስተኛ ወጪ በራስ አቅም የተገነቡ መሆናቸውን ጠቅሰው ሰራዊቱ ለሀገርና ለህዝብ ለሚከፍለው መስዋእትነት እውቅና የሚሰጡ በመሆናቸው ተግባሩ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ ከመኖሪያ ቤት ባለእድለኞች መካከል ሌተናል ኮሎኔል ታመነች ተሰማ እና ሌተናል ኮሎኔል አክሊሉ አሻንጎ የቤት ባለቤት በመሆናቸው ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸው፤ መንግስት ሰራዊቱን የቤት ባለቤት ለማድረግ የጀመረው ስራ የሚደነቅ ነው ብለዋል፡፡ ይህም ሰራዊቱ ራሱንና ቤተሰቡን በተረጋጋ ሁኔታ እንዲመራና ግዳጁን በተገቢው እንዲወጣ የሚያስችልና ተስፋን የሚሰጥ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በመርሃ ግብሩ ላይ የመከላከያ ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮች፣ የተለያየ ማዕረግ ያላቸው የሰራዊት አባላትና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።
መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭትን በማሳለጥ በኩል ከፍተኛ ለውጥ አስገኝቷል
May 23, 2026 199
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭትን በማሳለጥ በኩል ከፍተኛ ለውጥ ማስገኘቱን ኢዜአ ያነጋገራቸው አሽከርካሪዎች እና የነዳጅ ማደያዎች ገለጹ፡፡ በመካከለኛው ምስራቅ ተከስቶ የነበረውን ችግር ተከትሎ በዓለም አቀፍ ደረጃ በነዳጅ ምርት አቅርቦት ላይ የተፈጠረው ክፍተት፣ በሀገር ውስጥም የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል አስከትሎ የነበረ ቢሆንም፤ መንግሥት አቅርቦቱ ከጦርነቱ በፊት ወደነበረበት ደረጃ እንዲመለስ አድርጓል። መንግሥት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ የነበረውን ዓለም አቀፍ ተጽዕኖ ተቋቁሞ ለማለፍ ያስቻለ ሲሆን፣ አሁን ላይ በተለያዩ ከተሞች የተረጋጋ፣ ቀልጣፋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት እንዲኖር አስችሏል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ሚያዝያ 21 ቀን 2018 ዓ.ም በወቅታዊ የዓለም የነዳጅ ሁኔታን በማስመልከት በሰጡት ማብራሪያ፣ የናፍጣ ነዳጅ አቅርቦት ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት ወደነበረበት እንዲመለስ መደረጉን መጥቀሳቸው ይታወቃል፡፡ ኢዜአ በመዲናዋ ያነጋገራቸው አሽከርካሪዎችና የነዳጅ ማደያ ባለቤቶች፤ መንግሥት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደውን የማሻሻያ እርምጃ ተከትሎ በአቅርቦቱና በስርጭቱ ላይ ከፍተኛ አዎንታዊ ለውጥ መታየቱን ገልጸዋል። አስተያየት ከሰጡ አሽከርካሪዎች መካከል አባይነህ ይሁኔ፤ ቀደም ሲል ከዓለም አቀፉ የነዳጅ እጥረት ጋር ተያይዞ በነበረው መስተጓጎል በእለት ተእለት እንቅስቃሴያቸው ላይ ከፍተኛ ችግር ገጥሟቸው እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ላይ ግን የነበረው ችግር ሙሉ በሙሉ ተፈትቶ ሁኔታው ወደ ቀድሞው በመመለሱ፣ በሁሉም ማደያዎች የሚፈልጉትን ያህል ነዳጅ ያለምንም እንግልት እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ሌላኛው አሽከርካሪ ከድር ሁሴን በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል ነዳጅ ለማግኘት እስከ አንድ ሳምንት ይወስድባቸው የነበረው አስቸጋሪ ሁኔታ በአሁኑ ወቅት ሙሉ በሙሉ መፈታቱንና ያለምንም እንግልት ነዳጅ እያገኙ ማኅበረሰቡን በሚገባ እያገለገሉ መሆናቸውን አስረድተዋል። በተመሳሳይ አሽከርካሪ ተፈሪ ዓለሙ እና ረታ ጂቢቲ እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል ተከስቶ የነበረው የነዳጅ እጥረትና የረጅም ሰዓት ወረፋ በመንግሥት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት በመቀረፉ፣ በአሁኑ ወቅት ያለምንም መስተጓጎል እየተስተናገዱ ይገኛሉ። በነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ላይ የነበረው ችግር በመወገዱ በአሁኑ ወቅት የተረጋጋ ሁኔታ መፈጠሩንና መደበኛ ሥራቸውን በተሻለና ይበልጥ ውጤታማ በሆነ መልኩ እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። የነዳጅ ማደያ ሱፐርቫይዘሮች በበኩላቸው ቀደም ሲል በዓለም አቀፍ የነዳጅ ቀውስ ምክንያት ይፈጠር የነበረው የአቅርቦት ችግር በመቀረፉ ደንበኞቻቸውን ያለምንም እንግልት እያስተናገዱ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በአቅርቦትና በስርጭት ላይ ችግር አለመኖሩን ጠቁመው ለማኅበረሰቡ ጥሩ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በቡልጋሪያ አካባቢ የቶታል ማደያ ሱፐርቫይዘር ሰለሞን ገብረሕይወት እና በአሮጌው ቄራ አካባቢ ቶታል ማደያ ሱፐርቫይዘር ይርጋ ኪዳነ ማርያም ቀደም ሲል በነበረው እጥረት ምክንያት ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ለማግኘት እስከ አምስት ቀናት የሚደርስ ረጅም ሰልፍ ይጠብቁ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ላይ ችግሩ ሙሉ በሙሉ መቀረፉን አረጋግጠዋል። በተመሳሳይ የሜክሲኮ አካባቢ የካምፖ አስመራ ነዳጅ ማደያ ሱፐርቫይዘር ጥበቡ በቀለ በበኩላቸው፤ መንግሥት ዓለም አቀፉን የነዳጅ አቅርቦት ቀውስ ለማስተካከል የወሰደውን ቁርጠኛ እርምጃና የመጣውን ፈጣን አዎንታዊ ለውጥ አድንቀዋል። በአሁኑ ወቅት ነዳጅ ለማደያቸው በአግባቡና በወቅቱ እየቀረበ መሆኑን ገልጸው እያገኙት ያለውን ምርትም ለተጠቃሚ አሽከርካሪዎች እያቀረቡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።