ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ የመሰረተ ልማት ስኬት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፉን የሚያሳልጥ ወሳኝ ዕድል ፈጥሯል
Apr 18, 2026 300
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የመሰረተ ልማት ስኬት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፉን የሚያሳልጥ ወሳኝ ዕድል መፍጠሩን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክ ሚኒስትር ዴኤታ ዴንጌ ቦሩ ገለጹ። ''ኢትዮጵያ ትገነባለች፤ ፈጠራ፣ ፍጥነትና ጥራት ለመሰረተ ልማት እመርታ'' በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ የመሰረተ ልማትና ኮንስትራክሽን ሳምንት እየተካሄደ ይገኛል።   በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ሁለተኛ ቀኑን ይዞ በቀጠለው መድረክ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መሰረተ ልማት ትስስርና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ውይይት ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ዴንጌ ቦሩ፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ስኬቶች ተመዝግበዋል ብለዋል። እነዚህ ስኬቶችም የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ውጤታማነትን በማሻሻል አዲስ የኢኮኖሚ ዕድገት የለውጥ ምዕራፍ መክፈቱን ገልጸዋል። በቀጣይም የተቋማትን ቅንጅት በማጠናከር የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ትስስርን የሚያሳልጡ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።   የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መሀመድ አብዱራህማን የኢትዮጵያ መንገዶች ግንባታ እስከ ኤክስፕረስ መንገድ ያለው ዕምቅ አቅምና ቀጣይ ተስፋ የሚል የመነሻ ጽሁፍ አቅርበዋል። በጽሑፋቸውም፤ የኢትዮጵያ መንገዶች እ.አ.አ. በ1997 ከነበረበት 26 ሺህ 550 ኪሎ ሜትር በ2025 ከ180 ሺህ ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ጥራት ያለው የመንገድ መሰረተ ልማት መገንባቱን አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ የመንገድ ልማት ሽፋንም ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን በማፋጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም የመንግስት፣ የልማት አጋሮችንና ዓለም አቀፍ ተቋማትን የበጀት ትብብር በማጠናከር እ.አ.አ በ2030 የመንገድ ሽፋንን 245 ሺህ ኪሎ ሜትር ለማድረስ እየተሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል።   የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር ህሊና በላቸው፤ የኢትዮጵያን የባቡር ልማትና ቀጣናዊ ትስስር የሚዳስስ የመወያያ ጽሁፍ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ የኤሌክትሪክ ኃይል የባቡር መሠረተ ልማት የኢኮኖሚ ዕድትን በማፋጠን ቀጣናዊ ኢኮኖሚ ትስስርን ለማጠናከር የማይተካ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። በቀጣይም የባቡር መሰረተ ልማት ሥራዎችን የሚያፋጥን ብቁ የሰው ሃይል ለማፍራት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።   በመድረኩ በገጠር ትስስር ዙሪያ የመወያያ ጽሁፍ ያቀረቡት መሀመድ አሚን በበኩላቸው፤ የከተማና ገጠር ማህበራዊና ኢኮኖሚያ ትስስርን የሚያጠናክር የመንገድ መሰረተ ልማት እየተገነባ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የመንገድ መሰረተ ልማት ትስስር የአርሶና አርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያሳለጠ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 95 ሺህ ወጣቶች በተለያዩ የስራ መስኮች ተሰማርተዋል
Apr 18, 2026 82
ነቀምቴ ፤ሚያዚያ 10/2018 (ኢዜአ)፡-በምስራቅ ወለጋ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 95 ሺህ ወጣቶች ተደራጅተው በተለያዩ የስራ መስኮች መሰማራታቸውን የዞኑ የስራ እድል ፈጠራ እና ክህሎት ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ባጩ ተስፋዬ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ጽሕፈት ቤቱ የሥራ አጥነትን ችግር በማቃለል የአምራች ኃይሉን የልማት ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየሠራ ይገኛል። በበጀት ዓመቱም ከ100 ሺህ የሚበልጡ ወጣቶችን በማደራጀት ወደ ሥራ ለማስገባት የታቀደ ሲሆን፣ እስካሁን ባለው ሒደት 95 ሺህ ወጣቶችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። ወጣቶቹ ከተሰማሩባቸው መስኮች መካከል ግብርና እና ማኑፋክቸሪንግን ጨምሮ ሌሎች የገቢ ማስገኛ ፕሮግራሞችን በአብነት ጠቅሰዋል። ወጣቶቹ በተሰማሩባቸው መስኮች ውጤታማ መሆን እንዲችሉም መንግሥት ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር እንዳመቻቸላቸው ተናግረዋል። ይህም የዞኑን ወጣቶች የሥራ ባሕል በመቀየር የልማት ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ መደላድል መፍጠሩን ገልጸዋል። በዞኑ የሲቡ ስሬ ወረዳ የንግድ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ኢንቨስትመንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኢብሳ ዲለንሳ በበኩላቸው፤ ወጣቶች ከጠባቂነት ተላቀው ባላቸው ዕውቀት እና ጉልበት ሠርተው እንዲለወጡ በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህ ረገድ በበጀት ዓመቱ ከ9 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለማመቻቸት ታቅዶ ሲሠራ መቆየቱን ጠቅሰዋል። ወጣቶቹን በ340 ኢንተርፕራይዞች በማደራጀት በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በእንስሳት ማደለብና እርባታ፣ እንዲሁም በሌሎች መስኮች በመሰማራት የተሻለ ውጤት በማምጣት ላይ እንደሚገኙ አስረድተዋል። የወረዳው አስተዳደርም ከ37 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር በማቅረብ ኢንተርፕራይዞቹ እንዲጠናከሩ ድጋፍ ማድረጉን አብራርተዋል። ከሥራ ዕድሉ ተጠቃሚዎች መካከል በብረታ ብረትና እንጨት ሥራ የተሰማራው ጪምዴሳ በዳሳ እንደሚለው፤ በዚህ ዓመት መንግሥት ባመቻቸላቸው ዕድል የ200 ሺህ ብር ብድር በመውሰድ ሥራ ጀምረዋል። በተመቻቸላቸው ዕድል ጠንክረው በመሥራትም ከራሳቸው አልፎ ለሌሎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ይናገራል። በአሁኑ ወቅትም ካፒታላቸውን ወደ 1 ሚሊዮን ብር በማሳደግ ተጠቃሚ መሆናቸውን አመልክቷል። በወረዳው የሚገኙት የጫልቱ፣ ዓለምነሽ እና ጓደኞቻቸው ማህበር አባል ወጣት ምቲኬ አበራ፤ በተያዘው ዓመት በእንጀራ ንግድ ላይ ሥራ የጀመረው ማኅበራቸው ጥሩ ገቢ ማግኘት መጀመሩን ተናግራለች።  
በአምቦ ከተማ ከ900 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች ወደ ሥራ ገብተዋል
Apr 18, 2026 119
አምቦ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በአምቦ ከተማ በዘጠኝ ወራት ከ900 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ወደ ስራ መግባታቸውን የከተማ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በአምቦ ከተማና አካባቢው በተለይም የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴውን በተመለከተ የከተማ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጂፋራ ጫልችሳ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። ከለውጡ በኋላ በዘርፉ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በርካታ ባለሃብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች በመሳተፍ ለብዙ ወገኖች የስራ እድል እየፈጠሩ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በማኑፋክቸሪንግ፣ በአግሮ እንዱስትሪ፣ በአገልገሎት እና ሌሎችም መስኮች በብዛት እየተሳተፉ መሆኑን አንስተው፤ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራትም ከ900 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች ወደ ስራ ገብተዋል ብለዋል። ከከተማዋ መዘጋጃ ቤት ጋር በመተባበር የመሰረተ ልማትና የመሬት አቅርቦት እንዲሁም ምቹ አገልግሎት እንዲኖር መሰራቱን አስታውሰው በዚህም አልሚዎች እየተበራከቱ መጥተዋል ብለዋል። በዘንድሮው በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ብቻ 42 ሄክታር መሬት ለአልሚዎች መሰጠቱን ለአብነት ጠቅሰዋል።
በዞኑ ሞዴል አርሶ አደሮችን ወደ ኢንቨስትመንት የማሻገር ስራ እየተሰራ ነዉ
Apr 18, 2026 118
ጅማ፤ ሚያዚያ 10/2018(ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ሞዴል አርሶ አደሮችን እና በጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጅተዉ ስኬታማ የሆኑ ማህበራትን ወደ ኢንቨስትመንት የማሸጋገር ስራ እየተካሔደ ነዉ። በጅማ ዞን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሰፋፋ የመጣዉን የመሠረተ ልማት ግንባታ ተከትሎ በኢንቨስትመንት የሚሰማሩ ባለሀብቶች ቁጥር እየጨመረ መሆኑም ተገልጿል። በተያዘው ዓመትም 1 ሺህ 680 ፕሮጀክቶችን ወደ ስራ ማስገባቱን የዞኑ ኢንቨስትመንት እና ኢንዱስትሪ ፅህፈት ቤት አመልክቷል። የፅህፈት ቤቱ ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ዘሊካ ቡላ ለኢዜአ እንደተናገሩት ፤በተያዘው ዓመት በጥቃቅንና አነስተኛ የተደራጁ 20 ማህበራት፣ 39 የህብረት ስራ ማህበራትን ጨምሮ በድምሩ 1 ሺህ 680 ፕሮጀክቶች ወደ ኢንቨስትመንት ገብተዋል። ወደ ኢንቨስትመንት ከገቡት 1 ሺህ 680 ፕሮጀክቶች ውስጥ ደግሞ 1 ሺህ 621 የሚሆኑት ሞዴል አርሶ አደሮች መሆናቸውን ነው የገለጹት፤ ወደ ኢንቨስትመንት የገቡት ባለሃብቶችም 4 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ መሆናቸዉንም ነው ያመለከቱት። ለኢንቨስትመንት ስራዉ 7 ሺህ 578 ሄክታር መሬት መሰጠቱን የገለፁት ስራ አስኪያጇ ለፕሮጀክቶቹ ተግባራዊነት ጠንካራ የሆነ ክትትልና ደጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑንም ጠቅሰዋል። በዞኑ ለኢንቨስትመንት መሬት ተረክበዉ ወደ ስራ መግባት ያልቻሉትን በመለየትም የፋይናንስ እና የሊዝ ማሽን አቅርቦት ችግር ያለባቸውን በመለየት ከባንክ ብድር የሚያገኙበትን ሁኔታ ለማመቻቸት እየተሰራ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ሙያዊ ክትትልና ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑን አመልክተው አስፈላጊዉ ድጋፍ ተደርጎላቸዉ ወደ ስራ መግባት ያልቻሉ ባለሀብቶች ፍቃዳቸዉ የሚሰረዝበት አሰራር ተግባራዊ እንደሚደረግም ነው የጠቀሱት። በሌላ በኩል በተቋም ደረጃ አገልግሎት አሰጣጥን የማዘመን እና የማቀላጠፍ ስራ ትኩረት የተሰጠዉ ሲሆን ፣ ከዚህ ቀደም የነበሩ የተንዛዙ አሰራሮችን በማስቀረት የተሻለ አገልግሎት እየተሰጠ ነዉ ብለዋል።  
በክልሉ ከ919 ሺህ የሚበልጡ ዜጎች በተለያዩ መስኮች የስራ እድል አገኝተዋል
Apr 18, 2026 94
ባህር ዳር፤ ሚያዚያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ከ919 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች በተለያዩ መስኮች የስራ እድል መፈጠሩን የክልሉ ስራና ስልጠና ቢሮ ገለጸ። ‎የቢሮው የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተር ፕራይዞች ልማት ዳይሬክተር አቶ ስላባት ሰውአገኝ ለኢዜአ እንደገለፁት ዜጎችን የስራ እድል ተጠቃሚ ለማድረግ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው። በዚህም በበጀት ዓመቱ አንድ ነጥብ አንድ ሚሊዮን ለሚጠጉ ዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር ግብ ተይዞ በተደረገ ሁሉን አቀፍ ጥረት በዘጠኝ ወሩ ለ919 ሺህ 475 ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልፀዋል። የስራ ዕድሉ ከተፈጠረባቸው መስኮች መካከልም ከ125 ሺህ 300 በላይ የሚሆኑት በውጭ ሀገር የስራ ስምሪት መሆኑን ገልጸዋል። የስራ ዕድሉ በግብርና፣ በኢንዱስትሪና በአገልግሎት ዘርፎች መሆኑን ገልጸው፤ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት በድምሩ ለ919 ሺህ 475 ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል። ዳይሬክተሩ እንዳሉት 1 ሺህ 347 የመስሪያ ሼዶች እንዲሁም ለከተማ ግብርና፣ ለማዕድን ማውጫና ለሌሎች የግብርና ልማት ተግባራት 11 ሺህ 444 ሄክታር መሬት ለኢንተርፕራይዞች መተላለፉንም ተናግረዋል። ‎የመስሪያ ገንዘብ ለሚያስፈልጋቸው ኢንተርፕራይዞች ከ5 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ የብድር አቅርቦት የተመቻቸ ስለመሆኑም አንስተዋል።
በአማራ ክልል የበልግ ወቅት እስካሁን ከ241 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ ሰብሎች እየለማ ነው
Apr 18, 2026 85
ደሴ ፤ሚያዚያ 10/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የበልግ ወቅት እስካሁን ከ241 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ ሰብሎች መልማቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ ግብርና ቢሮ የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማንደፍሮ አስላከ (ዶ/ር)፤ በክልሉ ምርታማነትን ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትንና የዘንድሮውን የበልግ ወቅት ልማት በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በማብራሪያቸውም የክልሉን የግብርና ዘርፍ በማዘመን ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥና ከተረጅነት የመውጣት ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። በያዘነው የበልግ ወቅት ከ245 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት መታቀዱን አስታውሰው እስካሁን ከ241 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ ሰብሎች መሸፈን ተችሏል ብለዋል። አሁን እየጣለ ያለው የበልግ ዝናብ ለሰብል ልማት ተስማሚ በመሆኑ በተለይም የስንዴ፣ ገብስ፣ ጤፍ፣ ቦለቄ፣ ማሾ፣ አተር፣ ምስርና ሌሎችንም ሰብሎች መዝራት ስለመቻሉ ተናግረዋል። የልማት ጥረቱ ተጠናክሮ መቀጠሉን የገለጹት ዶ/ር ማንደፍሮ በበልጉ የተያዘውን እቅድ ለማሳካት የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የሰሜን ሽዋ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ ችሮታው አስፋው፤ በዞኑ ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የአካባቢውን ምቹነት መሰረት ያደረጉ የግብርና ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የበልጉን ዝናብ በመጠቀም በዞኑ እስካሁን ከ86 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን ጠቅሰው ከዚህም ከ1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት የሚገኝ ይሆናል ብለዋል። በደቡብ ወሎ ዞን የተሁለደሬ ወረዳ እና በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ደዋጨፋ ወረዳ የኢዜአ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አርሶ አደሮች በዘንድሮው የበልግ ውቅት የእስካሁኑ እንቅስቃሴ ጥሩ መሆኑን አንስተው ከፍተኛ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በመጪው ክረምት ሚተከሉ ከ916 ሺህ በላይ የቡና ችግኞች ተዘጋጅተዋል
Apr 18, 2026 102
ደብረ ማርቆስ ሚያዚያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን በመጪው ክረምት ሚተከሉ ከ916 ሺህ በላይ የቡና ችግኞች መዘጋጀታቸው ተገለፀ። በዞኑ ግብርና መምሪያ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ባለሙያ አቶ ተሾመ በላይ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤ በመጪው የክረም ወር ከ320 ሄክታ በላይ በሆነ መሬት ላይ የሚተከሉ 916 ሺህ የቡና ችግኞች ተዘጋጅተዋል። በዋናነትም የአካባቢውን ስነ ምህዳርና የአየር ንብረት ተስማሚነት በማረጋገጥ ለቡና ልማት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ገልፀዋል። በቡና ልማቱም ከ25 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ ከ320 ሄክታር በላይ መሬትን ለመሸፈን ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። ችግኞቹ በመንግስት፣ በማህበራትና በግለሰቦች የችግኝ ጣቢያዎች ፈልተው የተዘጋጁ መሆኑንም ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩን በተለያዩ የግብርና አማራጮች በማሳተፍ የምግብ ዋስትናውን ለማረጋገጥ እንዲችል ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ገልፀዋል። በዞኑ በደብረ ኤሊያስ፣ በማቻከልና በጎዛምን ወረዳዎች በኩታ-ገጠም እየተካሄደ ያለውን የቡና ልማት በማጠናከር በቀጣይ በሁሉም ወረዳዎች ተደራሽ የማድረግ ተግባራት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በማቻከል ወረዳ የውላ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አብነት ይርዳው፤ ቡናን በኩታ ገጠም ለማልማት ከግማሽ ሄክታር በላይ መሬት እያዘጋጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ገነት አያሌው በበኩላቸው ከዚህ ቀደም ካለሙት ቡና እያገኙ ያለውን ጥቅም ለማስፋት በክረምቱ የሚተከል ከሩብ ሄክታር በላይ ማሳቸውን እያዘጋጁ መሆናቸን ገልጸዋል። ለዚህም ከ6 ሺህ በላይ የቡና ችግኞችን ማፍላታቸውን ጠቁመው ከራሳቸው የሚተርፈውን በመሸጥ ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት አቅደው እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት በተደረገ ጥረት ከ5 ሺህ 300 ሄክታር በላይ መሬት በቡና መልማቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ሕይወትን መለወጥ እንደሚቻል በተግባር እያረጋገጠ ያለው የከተማ ግብርና
Apr 17, 2026 377
የሌማት ትሩፋት አካል በሆነው የከተማ ግብርና በመሰማራት ሕይወትን መለወጥ እንደሚቻል በተግባር እያሳየን ነው ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው በዘርፉ የተሰማሩ የመዲናዋ ነዋሪዎች ገለፁ። የከተማ ግብርና በከተማ ውስጥ በሚገኙ አነስተኛ ቦታዎች፣ መኖሪያ ግቢዎች፣ ጣራዎች ወይም አጥሮች ላይ ቀላል ቁሳቁሶችንና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም አትክልት፣ ፍራፍሬ፣ እንስሳትና ዓሳ በማምረት ህይወታቸውን የሚቀይሩበት የምርት ስርዓት ነው። ይህ ዘርፍ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የኑሮ ውድነትን ከመቀነስ ባለፈ ለሴቶችና ለወጣቶች ሰፊ የስራ ዕድልን በሰፊው የሚፈጥር ነው፤ በመፍጠር ላይም ይገኛል። መንግሥት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ወደ ተግባር የገባው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርም በገጠርም ሆነ በከተማ ዜጎች የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ በማድረግ ረገድ አመርቂ ውጤቶችን በማስመዝገብ ላይ ነው። በአዲስ አበባ በከተማ ግብርና የተሰማሩ ተጠቃሚዎችም በዘርፉ መሰማራታቸው የዕለት ተዕለት የቤት ፍጆታቸውን ከመሸፈን አልፎ አዋጭ የገቢ ምንጭ በመሆን ሕይወታቸውን በተጨባጭ እየቀየረላቸው እንደሚገኝ ነው ለኢዜአ የሚገልጹት።   በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ላይ የተሰማራው የወልዳ ወሊኒ ማህበር ሰብሳቢ ተካልኝ ደበሌ በ2014 ዓ.ም መንግሥት ለከተማ ግብርና ስራ የሰጠውን ትኩረት ተከትሎ ማህበራቸው ወደ ከተማ ግብርና ስራ መግባቱን ይገልጻሉ። ማህበሩ በአሁኑ ሰዓት ሰባት አባላት ያሉት መሆኑን በመጠቆም የተለያዩ የአትክልት ምርቶችን በማምረት ለራስ ፍጆታ ከማዋል ባለፈ ለማህበረሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የከተማ ግብርና ስራ በስፋት ያላተለመደ ተግባር እንደነበረ አንስተው፤ አሁን ላይ በግብርና ስራ ላይ የሚሰማሩ ነዋሪዎች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን ያነሳሉ።   ሌላኛው በእንስሳት እርባታ ላይ የተሰማራው ወጣት አወቀ አበባው እንደሚለው ዶሮዎችንና የወተት ላሞችን በማርባት ተጠቃሚ በመሆን ላይ ነው። እንቁላል እና የተለያዩ ወተትና የወተት ተዋጽኦ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማህበረሰቡ በማቅረብ ገበያ የማረጋጋት ስራ እየሰሩ መሆኑን ይናገራል። በዘርፉ የተሰማሩት እነዚህ ተጠቃሚዎች፣ በከተማ ግብርና ተሰማርቶ ውጤታማ መሆን እንደሚቻል በተጨባጭ እያረጋገጡ መሆኑን ያስረዳሉ። ሌሎች ዜጎችም መልካም ተሞክሮዎችን በመቀመርና በአካባቢያቸው ያለውን ሀብት በመጠቀም፣ የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የገቢ ምንጫቸውን እንዲያሳድጉ ጥሪ አቅርበዋል።   በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የእንስሳትና ሀብትና መኖ ልማት ባለሙያ አሰፉ ሙላቱ እና የሆርቲካልቸር ባለሙያው ማሙሽ አሳምነው እንደሚሉት በመዲናዋ የከተማ ግብርና ስራ ባህል እየሆነ መምጣቱን ይገልጻሉ።   በዘርፉ የተሰማሩ አካላት የተሻሻሉ ምርት ዝርያዎችን መጠቀም እንዲችሉ፣ምርትን ሲያመርቱ ደህንነቱን በጠበቀ መልኩ እንዲሆን ሙያዊ እገዛዎችን እያደረጉ እንደሚገኙ ገልጸው፤ ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።    
በኢትዮጵያ የተስማሚነት ምዘና ድርጅት የሚሰጡ አገልግሎቶችን ዓለም አቀፍ ቅቡልነት የሚያረጋግጥ አቅም እየተፈጠረ ነው
Apr 17, 2026 340
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ የተስማሚነት ምዘና ድርጅት የሚሰጡ የፍተሻ፣ የኢንስፔክሽንና የሰርተፊኬሽን አገልግሎቶችን ዓለም አቀፍ ተቀባይነት የሚያረጋግጥ አቅም እየተገነባ መሆኑን የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መዓዛ አበራ ገለጹ። ኢንጂነር መዓዛ አበራ እንደገለጹት፤ ተቋሙ የሀገሪቱን ምርቶችና አገልግሎቶች የጥራት ደረጃ በማረጋገጥ በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማስቻል እየሰራ ነው። በአሁኑ ወቅትም 124 የላብራቶሪ ፍተሻ ወሰኖች በዕውቅና ሰጭ አካል ኦዲት ተደርጎ ውጤቱ እየተጠበቀ መሆኑን ገልጸዋል። በኢንፔክሽን ዘርፍ በተሰራ ስራም በግብርና ምርት፣ በታሸጉ ምግቦች፣ በኬሚካል፣ በዌር ሀውስና በሊፍት ኢንስፔክሽን 16 ወሰኖችን ማስጠበቅ እንደተቻለ ተናግረዋል። በዘንድሮው ዓመትም በታወር ክሬን፣ በቧንቧ ውሃ ናሙና እንዲሁም በዘይትና በዱቄት ቫይታሚን ማበልጸግ ዘርፎች ተጨማሪ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ለማግኘት ማመልከቻ መቅረቡን ጠቁመዋል። በሰርተፊኬሽን ዘርፍም 47 ነባር የዓለም አቀፍ ዕውቅናዎችን በማስጠበቅ በዘንድሮው ዓመት ብቻ በ16 አዳዲስ ወሰኖች ላይ ዕውቅና ማግኘት መቻሉን አስታውቀዋል። በተጨማሪም 23 ወሰኖችን በመለየት ለዓለም አቀፍ ዕውቅና የሚረዳ የሰነድ ዝግጅትና የአቅም ግንባታ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ አንስተዋል። በዘንድሮ ዓመትም በአሉሚኒየም፣ በቆርቆሮ፣ በሚስማርና በሴራሚክ ምርቶች ላይ አዲስ ዕውቅና መገኘቱን ተናግረዋል። በአካባቢ ጥበቃና በትምህርት አስተዳደር ሥርዓት የተገኘው ዓለም አቀፍ ዕውቅናም ድርጅቱ የሚሰጣቸውን አገልግሎት በማንኛውም ዓለም ተቀባይነት እንዲኖረው የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰዋል። በመጨረሻም ድርጅቱ ግቦችን ለማሳካት ከብሔራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት እንዲሁም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝ አብራርተዋል።
በድሬዳዋ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ልማቱን ለማጠናከር የተጀመረው ጥረት ይጠናከራል
Apr 17, 2026 317
ድሬዳዋ፣ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ በመሰብሰብ፣ የሕዝብን የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች የመፍታት ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ሀርቢ ቡህ ገለጹ። የድሬዳዋ አስተዳደር የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ እና የመጪው በጀት ዓመት የትኩረት መስኮች ላይ ያተኮረ ውይይት ተካሄዷል።   አቶ ሀርቢ ቡህ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት የገጠርና የከተማውን ነዋሪ መሠረታዊ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት የተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ ልማቶች አበረታች ናቸው። በተያዘው በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራትም የተቀመጡ የልማት ውጥኖችን በላቀ ደረጃ ዳር ለማድረስ የተከናወኑ ሰው ተኮር የልማት ሥራዎች ስኬታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። እነዚህን አበረታች ውጤቶች ይበልጥ ለማሳደግ፣ የገጠሩን አርሶ እና አርብቶ አደር የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ እንዲሁም ድሬዳዋን የኢንዱስትሪ፣ የኢንቨስትመንት እና የሎጀስቲክስ ማዕከል የማድረግ ጉዞን በውጤት ለመደምደም የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አሳስበዋል። የሚፈለገውን ለውጥና ውጤት ለማስመዝገብም የአስተዳደሩ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች የሚያመነጩትን ገቢ አሟጦ የመሰብሰብ ሥራ በቅንጅት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በሥራ አፈጻጸም ግምገማው ላይ እንደተመለከተው፤ በዘንድሮው ዘጠኝ ወራት 7 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ፣ የተሰበሰበው 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ወይም የዕቅዱን 80 በመቶ መሆኑን ገልጸዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሙሉካ መሐመድ፤ የተሰበሰበው ገቢ ከታቀደው ዕቅድና ኢኮኖሚው ከሚያመነጨው ሀብት አንጻር አነስተኛ መሆኑን አንስተዋል።   የአስተዳደሩን ነዋሪዎች የልማት ጥያቄዎች በተሻለ ደረጃ ለመፍታትና ብልጽግናን ለማረጋገጥ በቀሪዎቹ ሦስት ወራት ገቢን አሟጦ የመሰብሰብ ጉዳይ በትኩረት መሠራት ይኖርበታል ብለዋል። ሌሎች የውይይቱ ተሳታፊዎችም በዘጠኝ ወራቱ በገጠርና በከተማ የተሠሩ ሰው ተኮር ልማቶች የሕዝብን አንገብጋቢ ጥያቄዎች በመፍታት ነዋሪው በልማቱ ላይ የባለቤትነት ተሳትፎውን እንዲያሳድግ ማስቻሉን ጠቁመዋል። በቀሪ የበጀት ወራት የተሻለ ሥራ በመሥራት የሚጠበቀውን ውጤት ለማስመዝገብ በቁርጠኝነት እንደሚተጉም አረጋግጠዋል።  
በአማራ ክልል ከመኸር እርሻ ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሰብል ምርት ለማግኘት ወደ ስራ ተገብቷል
Apr 17, 2026 158
ኮምቦልቻ፤ ሚያዚያ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ከመኸር እርሻ ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሰብል ምርት ለማግኘት ወደ ስራ መገባቱን በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የክልሉ ገጠር ዘርፍ አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) ገለፁ። የክልሉ ግብርና ቢሮ የ2018/19 መኸር ምርት ዘመን የሰብል ልማትና ጥበቃ ንቅናቄ መድረክ በኮምቦልቻ ከተማ አካሄዷል።   በመድረኩ ላይ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) እንደገለፁት፤ በተሻሻሉ አሰራሮች የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ለገበያ ለማቅረብ በትኩረት እየተሰራ ነው። ተግባሩን በማስቀጠልም በ2018/19 የመኸር ሰብል ልማት 5 ነጥብ 58 ሚሊዮን ሄክታር መሬትን በማልማት ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል። የመኸር ሰብሉን ውጤታማ ለማድረግም ለግብዓትና ለቴክኖሎጂ አቅርቦት ትኩረት በመስጠት ለምግብ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ሰብሎች በስፋት እንደሚመረቱ ተናግረዋል። ለዚህም የአደረጃጀት፣ የኩታ-ገጠም ልማት፣ የቴክኖሎጂ እና ሌሎች ዘመናዊ አሰራሮችን መተግበር እንደሚገባም አመልክተዋል።   የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ በበኩላቸው፣ በቴክኖሎጂና በተሻሻለ አሰራር ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በክልሉ በሰብል ልማት እየተመዘገበ የመጣውን ምርታማነት በማጠናክር በሄክታር 36 ነጥብ 3 ኩንታል ለማድረስ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ለዚህም የግብዓት አቅርቦት፣ የእርሻ ማሳ ዝግጅት፣ የባለሙያ ስልጠናና ሌሎችም ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው ለዘንድሮው የመኸር ሰብል ልማት እየተደረገ ካለው የእርሻ ዝግጅት በተጨማሪ ግብዓት በስፋት እየተሰራጨ ነው ብለዋል። በተሻሻለ አሰራር ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ምርት ለኢንዱስትሪዎችና ለገበያ ለማቅረብ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል። በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን ከ561 ሺህ ሄክታር በላይ መሬትን በማልማት ከ19 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ዝግጅት እየተደረገ ነው ያሉት ደግሞ የሰሜን ሽዋ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ችሮታው አስፋው ናቸው። አሲዳማ መሬትን በማከም፣ በኩታ-ገጠም በማልማት፣ በመስመር በመዝራትና ሌሎችንም የምርት ማሳደጊያ ቴክኖሎጂዎች በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራሮች፣ የግብርና ባለሙያዎችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።  
መሠረተ ልማት የኢኮኖሚው የደም ሥር እና የብልጽግና መሠረት ነው -ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 17, 2026 842
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ መሠረተ ልማት የኢኮኖሚው የደም ሥር፣ የብልጽግናም መሰረት ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ኢትዮጵያ እየተገነባች ነው በሚል መሪ ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ የተዘጋጀውን የኢትዮጵያ የመሠረተ ልማት እና ኮንስትራክሽን ሳምንት ዛሬ ከፍተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው መሠረተ ልማት ለሀገር ዕድገት ወሳኝ ግብአቶችን በማመላለስ የኢኮኖሚው የደም ሥር እና የብልጽግና መሠረት መሆኑን ገልጸዋል።   በዐውደ ርዕዩ የተመለከቱትም ወሳኝ የልማት ተቋማት መሠረተ ልማትን እንደ ሀገር በቅንጅትና በትብብር የመምራት አዲስ የሥራ ባህል እየገነቡ መሆናቸውን አመልክተዋል። ባለፉት ዓመታት ፈጠራን፣ ፍጥነትን እና ጥራትን የጉዞ መርሕ በማድረግ ተጨባጭ ስኬቶች መመዝገባቸውን ነው የገለጹት። የመንገድ ርዝመት በብዙ ኪሎ ሜትሮች ማደጉን፣ የታዳሽ ኃይል የማመንጨት ዐቅም ወደ 10 ሺህ ሜጋ ዋት አካባቢ መድረሱን፣ እንዲሁም በዲጂታል ዘርፍ የሞባይል ተጠቃሚዎች 97 ሚልዮን፣ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ደግሞ 57 ሚልዮን መድረሳቸውን በዝርዝር አቅርበዋል። በአዲስ አበባና በሌሎች ከተሞች የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ከተባበርን የማይቻል የለም የሚለውን መርሕ በተግባር ያሳዩ፣ ፍጥነትና ጥራትን ያስተሣሠሩ ፕሮጀክቶች መሆናቸውንም አክለዋል። የመንግሥትን የልማት ጉዞ ለማጣጣል ለሚሞክሩ አካላት እውነታውንና ፍርዱን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ትተን ሥራችንን እንቀጥላለን ሲሉም ተናግረዋል። ኢትዮጵያን ለማበልጸግና ለመገንባት በየበረሃውና በየተራራው እየፈሰሰ ላለው ላብና ደም ተገቢውን ክብር እንሰጣለን ነው ያሉት በመልዕክታቸው። መንግሥት በመንገድ፣ በኃይል፣ በመስኖ፣ በባቡርና በዲጂታል መሠረተ ልማት ዘርፍ ፈጣንና ፍትሐዊ ልማት ለማረጋገጥ የሚሠራውን ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። አሁን ያለንበት ወቅት የሥራ፣ የውጤት እና የተስፋ ዘመን መሆኑን በመጥቀስ፤ ትናንት የተገነባው ለዛሬ፣ ዛሬ የሚገነባው ደግሞ ለነገው ትውልድ ኩራት እና የብልጽግና ዋስትና መሆኑን አስገንዝበዋል።  
የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያሳልጡ መሠረተ ልማቶች በልዩ ትኩረት እየተገነቡ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 17, 2026 523
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያሳልጡ መሠረተ ልማቶች በልዩ ትኩረት እየተገነቡ እንደሚገኝ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ''ኢትዮጵያ ትገነባለች፤ ፈጠራ፣ ፍጥነት እና ጥራት ለመሰረተ ልማት እመርታ'' በሚል መሪ ሀሳብ የኢትዮጵያ የመሠረተ ልማትና ኮንስትራክሽን ሳምንት በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ዛሬ ተከፍቷል።   መድረኩን በይፋ የከፈቱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፤ ኢትዮጵያ አሁን ላይ የሥራ፣ የውጤት እና የተስፋ ዘመን ላይ ትገኛለች ብለዋል። የለውጡ መንግሥት የሚከተለው የመደመር ዕሳቤም ካለፈው መልካሙን በማስቀጠል፣ ዛሬን ተግቶ በመስራት ለነገ የሚተርፍ አሻራ ማሳረፍ መሆኑን ገልጸዋል። መሠረተ ልማትን በተቀናጀ መንገድ የመምራት አዲስ ባህል እየተፈጠረ መሆኑን ጠቁመው፤ በከተማና ገጠሩ ኢትዮጵያን ለማበልጸግ ዋጋ ለሚከፍሉ ወገኖች ክብር መስጠት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። መንግሥት የኢትዮጵያን ብልፅግና በፅኑ መሰረት ላይ ለማቆም እና ለማሳለጥ መሰረተ ልማትን በልዩ ትኩረት እያጠናከረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ከልማትና ብልፅግና ጉዟችን ለአፍታም አንዘናጋም ነው ያሉት። በኢትዮጵያ እየታየ ያለው ለውጥ ተሞክሮ የሚወሰድበት መሆኑን ያነሱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በአንጻሩ ለውጡን የሚያጣጥሉ ወገኖች መኖራቸውን ጠቅሰዋል።   ለእነዚህ ወገኖችም እኛ እነሱን ለማስረዳት የምናጠፋው ጊዜ የለም፤ ስራችንን እንቀጥላለን፤ እውነታውንና ፍርዱን ለኢትዮጵያ ህዝብና ለእውነተኛ ፈራጆች እንተዋለን ሲሉ ገልጸዋል። መሠረተ ልማት የኢኮኖሚ ዕድገት የደም ሥር መሆኑን በመግለጽ፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት አስደማሚ ስኬቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል። ​በመንገድ ሽፋኑም ከ126 ሺህ ኪሎ ሜትር ወደ 182 ሺህ ኪሎ ሜትር ማደጉን፣ በአቪዬሽን ዘርፍም ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብቱ የላቁ ስኬቶች መመዝገባቸውን አስረድተዋል። በታዳሽ ኃይል ልማት፣ በዲጂታል ተደራሽነትና በኮሪደር ልማት ዘርፎችም የኢትዮጵያን የዕድገት ጉዞ የሚያፋጥኑ እመርታዊ ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰዋል። በኮንስትራክሽን ዘርፍ የሚታዩ የጊዜ፣ የጥራትና የወጪ ውስንነቶችን ለመቅረፍ የተወሰዱ የፖሊሲና የሕግ ማዕቀፎችም የዘርፉን ውጤታማነት በማስጠበቅ ስኬት መገኙቱን አብራርተዋል። የመንግሥት ከፕሮጀክት ግንባታ ወደ ሥርዓት ግንባታ የተሸጋገረበት ስልታዊ አቅጣጫም ለሀገራዊ ብልፅግና ጉዞ ስኬት መሠረት መሆኑን ገልጸው፤ ይህ የኮንስትራክሽን ሳምንትም የመደመር መንግሥትን የልማት እይታና ሀገራዊ ራዕይ ያስተሳሰረ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል።
በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ስራ አቁመው የነበሩ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ወደ ስራ ማስገባት ተችሏል
Apr 17, 2026 72
ጎንደር፤ ሚያዚያ 9/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ስራ አቁመው የነበሩ በርካታ አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ፡፡ ''እኛም እንሸምት'' በሚል መሪ ሃሳብ በጎንደር ከተማ ሲካሔድ የቆየው ኢትዮጵያ ታምርት የንቅናቄ መድረክ የማጠቃለያ መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡   የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ተፈራ ታረቀኝ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ አምራች ኢንዱስሪዎች የሚያነሷቸውን ችግሮች በመፍታት ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል። በዚህም ባለፉት 9 ወራት ውስጥ ማምረት ያቆሙና ወደ ማምረት ያልገቡ 137 ከፍተኛና መካከለኛ አምራች ኢንዱስሪዎች ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉን አመልክተዋል። በዚሁ ወቅትም ሶስት ሺህ ለሚጠጉ ባለሀብቶችም የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠቱን ገልጸዋል።   ኢንዲስትሪዎቹ መሰረተ ልማቶች እንዲሟሉላቸው በማድረግ ፣የግንባታ ቦታዎችን በፍጥነት በማቅረብና የፋይናንስ ችግሮቻቸውን በመፍታትም ነው ስራ እንዲጀምሩ የተደረገው ብለዋል፡፡ በዚህም ለበርካታ ወገኖች የስራ እድል በመፍጠር ፣ ተኪና ለወጭ ንግድ የሚሆኑ ምርቶችን በማቅረብ በአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ እድገት ውስጥ የድርሻቸውን እንደሚወጡም ነው የገለጹት። በክልሉ ከ17ሺ በላይ ባለሀብቶችና ባለ ድርሻ አካላት የተሳተፉበት የኢትዮጵያ ታምርት የንቅናቄ መድረኮች መካሄዳቸውን ጠቁመው መድረኮቹም ችግሮችን ተቀራርቦ ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውንም ጠቅሰዋል። በጎንደር ከተማ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት በሚደረገው ጥረት ውስጥ 5 የኢንዱስትሪ መንደሮች ተቋቁመው ወደ ስራ መግባታቸውን የገለጹት ደግሞ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ናቸው፡፡ ጎንደር ከተማ በአግሮ ፕሮሰሲንግ፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ዘርፍ ለሚሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች ምቹና ተመራጭ መሆኑዋን ገልጸዋል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኃላፊ አቶ ግርማይ ልጃለም በበኩላቸው፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 10 መካከለኛና አንድ ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ ገብተዋል ነው ያሉት። በከተማው በኤክስፖርት ምርት የተሰማሩ 7 አምራች ኢንዱስትሪዎች 17ሺ ቶን ምርት ለውጭ ገበያ በማቅረብ 143 ሚሊዮን ዶላር የውጪ ምንዛሬ ማስገኘታቸውን ተናግረዋል፡፡   በተኪ ምርት የተሰማሩ 99 አምራች ኢንዱስትሪዎች 38 ሺህ ቶን የሚጠጋ ምርት በማምረት ከ149 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማዳን እንዳስቻሉም አመልክተዋል፡፡ በመድረኩ የተሳተፉ ባለሀብቶች በበኩላቸው ከተማ አስተዳደሩ በግንባታና በመሰረተ ልማት አቅርቦት ረገድ ያደረገላቸው ድጋፍ ፈጥነው ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ እንዳገዛቸው አስረድተዋል፡፡ በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችን ጨምሮ ባለሀብቶች ተሳታፊ ሲሆኑ አምራች ኢንዱስትሪዎች ምርቶቻቸውን ያቀረቡበት ኤግዚቢሽንም ተመርቆ ተከፍቷል፡፡
ስትራቴጂካዊ ፋይዳ ላላቸው ቀጣናዊ ኮሪደሮች የሚደረገው የገንዘብ ድጋፍ ሊጠናከር ይገባል- የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ
Apr 17, 2026 478
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ስትራቴጂካዊ ፋይዳ ላላቸው ቀጣናዊ ኮሪደሮች ፈጣን የፋይናንስ አቅርቦት እንዲመቻች አሳሰቡ። የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብስባ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ነው። 28ኛው የአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ የሚኒስትሮች ስብሰባም ጎን ለጎን ተካሂዷል።   የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ በሚኒስትሮች ስብሰባው ላይ ተሳትፈዋል። ከ130 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ላላትና የንግድ እንቅስቃሴዋ ሙሉ በሙሉ በቀጣናዊ ትስስር ላይ ለተመሰረተ አገር፣ ቀልጣፋ የትራንስፖርት ኮሪደሮች አማራጭ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ ነው ሲሉ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በኢኮኖሚ ኮሪደሮች ላይ የሚደረግ ፈጣን የኢንቨስትመንት ንግድን ለማቀላጠፍ፣ ተወዳዳሪነትን ለማጎልበት እና በቀጣናው የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። እነዚህን ኮሪደሮች ቀጣናዊ ዕድገት፣ ትስስርና ዕድል የሚፈጠርባቸው ዋነኛ ሞተሮች ለማድረግ በጋራ መሥራት እንደሚገባም አሳስበዋል። ለቀጣናዊ ኮሪደሮች የሚደረገው የገንዘብ ድጋፍ እንዲጠናከርም ሚኒስትሩ ጥሪ አቅርበዋል። ስብሰባው ከ9 ሺህ 100 ኪሎ ሜትር በላይ የሚሸፍኑ እና 3 ነጥብ 8 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት የተመደበላቸውን አራት ቅድሚያ የሚሰጣቸው ኮሪደሮች አፈጻጸም ገምግሟል። የልማት አጋሮች ከእ.አ.አ 2019 ጀምሮ ለኮሪደሮቹ ግንባታ የሚውል 2 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ድጋፍ አሰባስበዋል። ምንም እንኳን መሻሻሎች ቢታዩም፣ ቀጣናውን ሙሉ በሙሉ ለማስተሳሰር ወሳኝ በሆኑ የመንገድ ክፍሎች ላይ አሁንም የፋይናንስ ክፍተት መኖሩን ሚኒስትሮቹ አመልክተዋል። ውይይቱ ኢንቨስትመንትን በማሳደግ እና አፈጻጸምን ለማፋጠን በሚያስችሉ አዳዲስ የፋይናንስ አማራጮች ላይ ትኩረት አድርጓል። በስብሰባው ላይ የፋይናንስ ክፍተቶችን በመሙላትና ከፍተኛ ፋይዳ ያላቸውን የኮሪደር ፕሮጀክቶች በማፋጠን የቀጣናውን የኢኮኖሚ አቅም ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር እንደሚገባ የጋራ አቋም መያዙን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
የዘላቂ የዕዳ አስተዳደር የኢኮኖሚ ሪፎርሙ ስትራቴጂካዊ ትኩረት ነው -የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ
Apr 17, 2026 408
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዘላቂ የዕዳ አስተዳደርን የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ አካል አድርጋ እየሰራች እንደምትገኝ የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገለጹ። የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብሰባ በዋሺንግተን ዲሲ መካሄዱን ቀጥሏል።   የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ፣ ከስብሰባው ጎን ለጎን ዓለም አቀፍ የመንግስታት ዕዳ (Global Sovereign Debt) የተመለከተ ስብሰባ ላይ ተሳትፈዋል። ኢትዮጵያ በውይይቱ ወቅት፤ በዕዳ ውስጥ ባሉ አገራት፣ በሁለትዮሽ የመንግሥታት አበዳሪዎች፣ በግል አበዳሪዎች እና በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት መካከል ገንቢና ሁሉን አቀፍ ውይይት እንዲኖር መድረኩ ለሚጫወተው ሚና ያላትን አድናቆት ገልጻለች። ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ኢትዮጵያ በቡድን 20 (G20) የጋራ ማዕቀፍ አማካኝነት እያከናወነችው የሚገኘውን የዕዳ ሽግሽግ (debt restructuring) ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ ገለጻ አድርገዋል። የድርድር ሂደቱ ከአጋሮች ጋር ያለውን ጠንካራ ትብብር የሚያንፀባርቅ ከመሆኑም በላይ፣ መንግሥት የዕዳ ዘላቂነትን ለማረጋገጥና የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋትን ለማስፈን ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል። ሚኒስትሩ በገለጻቸው፤ የዕዳ ሽግሽግ ስምምነቱ ግቡን እንዲመታ የባለድርሻ አካላት የተቀናጀና ፈጣን ድጋፍ አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል። የሪፎርም ስራዎቿን ለማስቀጠልና ምጣኔ ሀብታዊ መረጋጋትን ለማረጋገጥ፤ ከአበዳሪዎችና ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት የሚጠበቀው ገንቢ ተሳትፎና ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ኢትዮጵያ ጥሪዋን አስተላልፋለች። ኢትዮጵያ የዘላቂ የዕዳ አስተዳደርን የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው አካል አድርጋ እየሰራች መሆኑንና ይህም የፊስካል ዲሲፕሊን፣ የሀገር ውስጥ ሀብት አሰባሰብ እና አካታች ዕድገት ላይ ትኩረት እንደሚያደርግ ገልጻለች። መንግሥት ስልታዊ የሆነ የዕዳ አስተዳደርን በመከተል፣ ከዕዳ ሽግሽግ የሚገኙ ዕድሎችን ለዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትና ለልማት ግቦች ለማዋል ያለውን ጽኑ አቋም በድጋሚ ገልጿል። ኢትዮጵያ በውይይቱ ላይ መሳተፏ በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ግንኙነቶች ያላትን ንቁ ተሳትፎና የዕዳ ተጋላጭነትን በጋራ ለመፍታት ከአለም አቀፍ አጋሮች ጋር ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አስታውቋል።
ኢትዮጵያ እና የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ኮርፖሬሽን ስትራቴጂካዊ አጋርነታቸውን ለማጎልበት ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ
Apr 17, 2026 154
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ኮርፖሬሽን ስትራቴጂካዊ አጋርነታቸውን ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሰሩ አስታወቁ። የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብስባ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ይገኛል። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ከስብሰባው ጎን ለጎን ከአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ኮርፖሬሽን (DFC) ዋና ሥራ አስፈጻሚ ቤን ብላክ ጋር የከፍተኛ ደረጃ ምክክር አደረጉ።   ውይይቱ በኢትዮጵያ እና በፋይናንስ ኮርፖሬሽኑ (DFC) መካከል ያለውን ስትራቴጂካዊ አጋርነት ማጠናከር ላይ ያተኮረ ሲሆን፣ በተለይም እንደ ትራንስፖርት እና ማዕድን ባሉ ቅድሚያ በሚሰጣቸው ዘርፎች ትብብርን ማስፋት ላይ የሀሳብ ልውውጥ አድርገዋል። ሁለቱ ወገኖች ዘላቂ እና አካታች እድገትን ለማፋጠን የልማት ፋይናንስ ያለውን ወሳኝ ሚና ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ የኢኮኖሚ እና የንግድ ትብብርን ማጠናከር በሚቻልባቸው መንገዶች ላይም መክረዋል። ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለችውን አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የኢንቨስትመንት ምህዳሩን ለማሻሻል የሚደረጉ ጥረቶችን አብራርተዋል። መንግስት ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ያለውን ቁርጠኝነትም አረጋግጠዋል። የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ኮርፖሬሽን (DFC) ግዙፍ ፕሮጀክቶች በተለይም በመሠረተ ልማት እና በሌሎች ስትራቴጂካዊ ዘርፎች በኢትዮጵያ ያለውን ተሳትፎ ለማሳደግ ያለውን ፍላጎት በድጋሚ ገልጿል። ሁለቱም ወገኖች የፋይናንስ ዕድሎችን ለመጠቀም እና የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ ውጤቶችን ለማምጣት የቀጣይ ትብብር አስፈላጊነትን አጽንኦት ሰጥተውበታል። ሁለቱ ወገኖች ትብብራቸውን ለማጠናከር እና በኢትዮጵያ ውስጥ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን የኢንቨስትመንት ኢኒሼቲቮች ለማሳለጥ የጋራ ቁርጠኝነታቸውን መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
በክልሉ ዘመናዊ የመስኖ አውታሮችን በማስፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው- ቢሮው
Apr 17, 2026 135
ባህር ዳር፤ ሚያዚያ 8/2018( ኢዜአ)፡-ዘመናዊ የመስኖ አውታሮችን ግንባታ በማስፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ገለፀ። በክልሉ ባላፉት ዘጠኝ ወራት አንድ ሺህ 131 ሄክታር መሬት ማልማት ያስቻሉ ዘመናዊ የመስኖ ተቋማት ተገንብተው ለአገልግሎት መብቃታቸው ተገልጿል። በክልሉ በመስኖ መልማት የሚችል ከ2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ያለ ቢሆንም እስካሁን በዘመናዊ መንገድ ወደ ልማት የገባው ከ242 ሺህ ሄከታር የሚበልጥ አይደለም።   የቢሮው የመስኖ ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ አየልኝ መሳፍንት ለኢዜአ እንዳሉት፤ የዘመናዊ የመስኖ ተቋማት ግንባታ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። በዚህም አርሶ አደሩን ከልማዳዊ አሰራር በማላቀቅ የዘመናዊ መስኖ ተጠቃሚ እንዲሆን የግንባታ ቦታዎችን በጥናት በመለየት ወደ ስራ ለማስገባት ሰፊ ጥረት እየተደረገ እንደሆነም ነው የገለጹት። ባለፉት ዘጠኝ ወራትም 23 መካከለኛና አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ አንድ ሺህ 131 ሄክታር መሬት ማልማት እንደተቻለ ገልፀዋል። በመስኖ ተቋማቱም ከ3 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለ ጠቅሰው፤ በአሁኑ ወቅትም ከ100 ያላነሱ የመስኖ ተቋማት ግንባታ እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልፀዋል። ለመስኖ ተቋማቱ ግንባታ ለተያዘው ዓመት ብቻ ከ4 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ተመድቦ እየተሰራ ሲሆን በቀሪ ወራትም ሌሎች በግንባታ ሂደት ላይ ያሉ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።   የዘመናዊ መስኖ መስፋፋት እንደ ሃገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማሳካት ተይዞ እየተከናወነ ያለውን ግብ ውጤታማ ለማድረግ በሚያስችል ሁኔታ እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል። የመስኖ ተቋማቱ ግንባታ ለበርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች የስራ ዕድል በመፍጠርም በኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እያስቻሉ መሆኑንም አንስተዋል። በክልሉ በወንዝ ጠለፋና መሰል ባህላዊ የመስኖ ልማት መንገድ 481 ሺህ ሄክታር መሬት እየለማ እንደሆነም ምክትል ቢሮ ኃላፊው ጨምረው ገልፀዋል።
በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር የክላስተር የፍራፍሬ ልማት ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ተከናወነ
Apr 17, 2026 171
ደዋጨፋ፤ሚያዝያ 9/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደና በአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ የሚመራ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ቡድን በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ደዋ ጨፋ ወረዳ በክላስተር የሚካሄድ የፍራፍሬ ልማት ችግኝ ተከላ አስጀምሯል። ከርዕሳነ መስተዳድሮቹ በተጨማሪ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር)፣ የአማራ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋዬ፣እንዲሁም በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር)ና ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ተገኝተዋል።   በተጨማሪም ሌሎች የክልል፣የዞን አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በመርሃ ግብሩ ታድመዋል። በክልሉ የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዋና አስተዳዳሪ አቶ አህመድ አሊ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፣የዞኑ ስነ-ምህዳርና የአየር ንብረት ለፍራፍሬ ልማት ምቹ ነው። ዞኑ በገፅና በከርሰ ምድር ውሃ የታደለ በመሆኑ ያለውን ጸጋ በመጠቀም የኩታ-ገጠም የፍራፍሬ ልማት ስራን በዛሬው እለት በይፋ መጀመሩን ገልጸዋል።   ይህም እስካሁን በተበጣጠሰ መልኩ ሲካሔድ የነበረውን የፍራፍሬ ልማት ወደ ኩታ ገጠም በማስፋት ለአገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ታልሞ እየተሰራ መሆኑን ያመላክታል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የአካባቢው አርሶ አደሮችን በማደራጀትና ግንዛቤ በመፍጠር የፍራፍሬ ልማት ስራ አዋጭ መሆኑን ከግንዛቤ አስገብተው ወደ ስራ እንዲገቡ እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም