ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጡ መሆኑን አመላካች ናቸው
Jun 26, 2026 819
አዲስ አበባ፤ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጡ እንደሚገኙ አመላካች መሆናቸውን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ። የገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ በበኩላቸው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ዘመናዊ የኢኮኖሚ አስተዳደር ሥርዓትን በመገንባት ረገድ ገንቢ ሚና ማበርከቱን ተናግረዋል። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 1ኛ ልዩ ስብሰባ በዛሬው ዕለት ተካሂዷል። ምክር ቤቱ ባካሄደው ልዩ ስብሰባ ከዓለም አቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተፈረሙ ሦስት የፋይናንስ ድጋፍና ብድር ስምምነት አዋጆችን አጽድቋል፡፡ የገንዘብ ሚኒስትሩ አሕመድ ሽዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ባለፉት ዓመታት የተተገበረው የተሟላ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የፋይናንስ ዘርፉን በማረጋጋት ረገድ አወንታዊ ሚና አበርክቷል፡፡ በተለይ ደግሞ የገቢ አሰባሰብንና የውጭ ምንዛሬ መጠንን በከፍተኛ መጠን ማሳደጉን ተናግረዋል፡፡ ሪፎርሙ ዘመናዊ የኢኮኖሚ አስተዳደር ሥርዓትን በመገንባት ረገድ ገንቢ ሚና መጫወቱንም ነው የገለጹት፡፡ ከዓለም አቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተፈረሙ የድጋፍና ብድር ስምምነቶች በፋይናንስ፣ በንግድ፣ በአየር ንብረት ለውጥ፣ በኢነርጂ፣ በመሠረተ ልማት፣ በግብርና እና በሌሎች ዘርፎች እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን ለመደገፍ የሚውሉ ናቸው ብለዋል፡፡ የወጣቶችን፣ ሴቶችን፣ የአርሶና አርብቶ አደሮችን ሕይወት ለማሻሻል በሚደረገው ርብርብ ትልቅ የፋይናንስ አቅም እንደሚፈጥሩም ጠቁመዋል። የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባትና የመስኖ ልማቶችን ለማዘመን እንደሚያግዙም እንዲሁ። የምክር ቤት አባላት በበኩላቸው፤ የድጋፍና የብድር ስምምነቶቹ ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ምን ያህል ለውጥ እያመጡና የሕብረተሰቡን ሕይወት በተጨባጭ እየቀየሩ በመሆኑ የተገኙ ናቸው ብለዋል። ለተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች መሳካትም ትልቅ የፋይናንስ አቅም እንደሚሆኑ ተናግረዋል፡፡ ምክር ቤቱ በልዩ ስብሰባው ከጤና፣ ማኅበራዊ ልማት፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የቀረበለትን ሪፖርት መርምሮ የምግብ ሥርዓትና ሥርዓተ ምግብ አዋጅን አጽድቋል፡፡ በተመሳሳይ ከግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የቀረበለትን የግብርና ቢዝነስ ካምፓኒ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ አጽድቋል፡፡ #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ኢትዮጵያ ቀጣናዊ መሰረተ ልማቶችን በመገንባት አህጉራዊ ኃላፊነቷን በብቃት እየተወጣች ነው
Jun 26, 2026 567
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያሳልጡ ወሳኝ መሰረተ ልማቶችን በመገንባት አህጉራዊ ኃላፊነቷን በብቃት እየተወጣች መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ ገለጹ። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ከአፍሪካ ሀገራት ጋር ያላቸውን የኢኮኖሚ፣ የኢንቨስትመንትና የጂኦፖለቲካዊ ትስስር ይበልጥ ለማሳደግ ያለመ "ሂሊ ዲያሎግ-አፍሪካ ኤዲሽን" የምክክር መድረክ ተካሂዷል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የምስራቅ አፍሪካ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ጌታቸው ረዳ በመድረኩ፤ ኢትዮጵያ ቀጣናዊ ትስስርን የሚያሳልጡ መሰረተ ልማቶችን በመገንባት ውጤታማ ስራ እያከናወነች ነው ብለዋል። በዚህም የምስራቅ አፍሪካ ሀገራትን በኤሌክትሪክ ኃይል፣ በመንገድና በመሳሰሉት መሰረተ ልማቶች በማስተሳሰር የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያሳልጥ ገንቢ ሚና እየተወጣች መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እስከ ታንዛኒያ ድረስ የኤሌክትሪክ መስመር በመዘርጋት የምትሰራው ውጤታማ የልማት ሥራም አህጉራዊ ኃላፊነቷን በብቃት እየተወጣች መሆኗን እንደሚያሳይ ተናግረዋል። የአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063ን ዕውን ለማድረግም አባል ሀገራት የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያሳልጡ መሰረተ ልማቶችን መዘርጋት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊና ቀጣናዊ የመሰረተ ልማት ውጤቶችም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ሀገራዊ ዕድገትን የሚያፋጥኑ መሆናቸውን አስረድተዋል። ለዲጂታል ኢኮኖሚ የተሰጠው ትኩረትም ንግድና ኢንቨስትመንትን በማሳለጥ ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ባለሃብቶች ጨምሮ ለውጭ አልሚዎች አስቻይ ምኅዳር መፍጠሩን አስረድተዋል። የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የስትራቴጂክ ጥናትና ምርምር ማዕከል ኢኮኖሚስትና ተመራማሪ መሐመድ አል አባቢ በበኩላቸው፤ አፍሪካ በሁሉም መስክ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ስትራቴጂክ አጋር ናት ብለዋል። በዚህም በምግብ ዋስትና፣ በታዳሽ ኃይልና ቁልፍ መሰረተ ልማት ግንባታ ዘርፍ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ትብብር በመፍጠር እየሰራች እንደምትገኝ ገልጸዋል።
በካፋ ዞን በዘንድሮ የመኸር እርሻ ከ126 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይለማል
Jun 26, 2026 223
ቦንጋ ፤ ሰኔ 19 /2018 (ኢዜአ)፦ በካፋ ዞን በዘንድሮ የመኸር አዝመራ ከ126 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት እንደሚለማ የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለፀ። የዞኑ ግብርና መምሪያ የ2018 ዓመተ ምህረት የግብርና ተግባራት አፈጻጸም ግምገማና የ2018/19 የመኸር ግብርና ስራዎች ዕቅድ ንቅናቄ መድረክ አካሄዷል። በመድረኩ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ ለግብርናው ዘርፍ የተሰጠውን ትኩረት በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ይበልጥ ለማሳደግ ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። ግብርና ሁሉን አቀፍ ለውጥ ለማስመዝገብ ወሳኝ ዘርፍ በመሆኑ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግና ዘመናዊ አሰራሮችን በመከተል ያለውን አቅም አስተባብሮ ወደ ስራ በመግባት የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ ይገባል ብለዋል። በዘንድሮው የመኸር እርሻ 126 ሺህ 491 ሄክታር መሬት ለማልማት መታቀዱን ገልፀዋል። በዚህም የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት በየደረጃው በቁርጠኝነት ይሰራል ያሉት አስተዳዳሪው፣ ለአረንጓዴ አሻራ፣ ለቡና ልማትና ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ልዩ ትኩረት ይሰጣል ነው ያሉት። የካፋ ዞን ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ሥራ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ገረመው ገብሬ በበኩላቸው በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ3 ሚሊዮን 225 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። ለዚህም የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን 40 በመቶ በማድረስና 30 በመቶ የሚሆነውን መሬት በክላስቴር በማልማት የታቀደውን ያህል ምርት ለማምረት ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። የግብዓት እጥረት እንዳይገጥም የተፈጥሮ ማዳበሪያ አጠቃቀም ላይ ትኩረት እንደሚሰጥ ያነሱት አቶ ገረመው የማይታረስ መሬትን ዜሮ በማድረስ የተያዘውን እቅድ ለማሳካት የድጋፍና ክትትል ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። በዘንድሮው የመኸር አዝመራ የተያዘውን እቅድ ለማሳካት ቴክኖሎጂን ከመጠቀም ባለፈ ለኩታ ገጠም እርሻ ትኩረት በመስጠት ምርታማነትን ለማሳደግ እንደሚሰሩ የገለፁት ደግሞ የጠሎና ወረዳ ዋና አስተዳደሪ አቶ አትርሴ ሸታቸው እና የሺሾ እንዴ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ደምሴ ገብረማርያም ናቸው። በ2017/18 የመኸር አዝመራ ከ123 ሺህ ሄክታር በላይ መሬትን በማልማት ከ2 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡንም ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው ልዩ ስብሰባ የተለያዩ የብድርና ድጋፍ ስምምነት አዋጆችን አጸደቀ
Jun 26, 2026 298
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው ልዩ ስብሰባ ከዓለም ዓቀፍ የልማት ማህበር ጋር የተፈረሙ ሶስት የፋይናንስ ድጋፍና ብድር ስምምነት አዋጆችን አጸደቀ፡፡ 6ኛው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 1ኛ ልዩ ስብሰባ በዛሬው እለት ተካሂዷል። ለምክር ቤቱ ከቀረቡት ስምምነቶች መካከል የመጀመሪያው ለዘላቂ እና ሁሉን አቀፍ የእድገት ልማት ፖሊሲ ማስፈፀሚያ የሚውል የአራት መቶ ሰላሳ ሰባት ሚሊዮን አራት መቶ ሺ (437,400,000) ኤስ.ዲ.አር የብድር ስምምነት ነው፡፡ ሁለተኛው የማህበረሰብ ተኮር የመሬት አያያዝ ፕሮግራም ማስፈፀሚያ የሚውል የአንድ መቶ አርባ አምስት ሚሊዮን አምስት መቶ ሺ (145,500,000) ኤስ.ዲ.አር የብድር ስምምነት ነው፡፡ ሶስተኛው ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የመስኖ ልማት ለዘላቂ ምርታማነት ፕሮጀክት ማስፈፀሚያ የሀምሳ አራት ሚሊዮን ስድስት መቶ ሺ (54,600,000) ኤስ.ዲ.አር የብድር ስምምነት ነው፡፡ ምክር ቤቱም እነኚህን የብድርና ድጋፍ ስምምነት አዋጆችን መርምሮ አጽድቋል። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ በዚሁ ወቅት፤ የብድርና ድጋፍ ስምምነቶች ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው የልማት ተግባራት ምን ያክል ለውጥ እያመጡ እና የህብረተሰቡን ህይወት በተጨባጭ እየቀየሩ መሆናቸውን የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙን ይበልጥ በማጠናከር፤ ወደ ውጪ የሚላኩ ምርቶችን በመጠንና በጥራት በማሳደግ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት አይነተኛ ሚና እንደሚኖራቸው ገልጸዋል። የወጣቶችን፣ ሴቶችን፣ የአርሶና አርብቶ አደሮችን ህይወት ለማሻሻል በሚደረገው ረብርብ ትልቅ የፋይናንስ አቅም እንደሚሆን ጠቁመዋል። የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባትና የመስኖ ልማቶችን ለማዘመን እንደሚያግዝም እንዲሁ።
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች ነው
Jun 26, 2026 215
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች መሆኑ ተገለጸ፡፡ የመንገድ ደህንነት መድን ፈንድ አገልግሎት በመንገድ ትራፊክ አደጋ የሚደርሰውን ሞት ፣ የአካል ጉዳትና የንብረት ውድመት ለመቀነስ በዘርፉ የተቀመጡ ሀገራዊና ዓለም አቀፋዊ ግቦችን ለማሳካት የግማሽ ዘመን ስትራቴጂ አፈፃፀም ላይ ሀገር አቀፍ ጉባኤ እያካሄደ ይገኛል። የኢትዮጵያ የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አባሶ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ ደህንነቱ የተጠበቀ የትራፊክ ፍሰት ለመፍጠር የተጀመሩ የስትራቴጂክ ስራዎች ተጨባጭ ፍሬ ማፍራት ጀምረዋል፡፡ አገልግሎቱ የትራፊክ አደጋ ስጋትን ለመቀነስ በቅንጅት ያከናወናቸው ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤት እያስገኙ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ በተከናወኑት ስልታዊ የቅድመ-መከላከል ስራዎች ምክንያት የአደጋው ቁጥር ጉልህ መሻሻል እያሳየ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ የወርልድ ሪሶርስ ኢንስቲትዩት (WRI) ከፍተኛ ባለሙያ ኢንጂነር ሰመረ ጅላሉ በበኩላቸው፤ ከ2021 እስከ 2030 የተቀመጡትን ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦች ለማሳካት በርካታ ስኬታማ ተግባራት ማከናወኗን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የመንገድ ደህንነት ግቦችን ከአገሪቱ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥማ እየተገበረች መሆኗን ገልጸዋል፡፡ በሕብረተሰቡ ዘንድ በትራፊክ አደጋ ተጋላጭነት ዙሪያ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች ሲከናወኑ የቆዩ ሲሆን፣ በቀጣይም ተግባራቱ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በመድረኩ ተጠቅሷል፡፡ በዚሁ ሀገር አቀፍ ጉባኤ ላይ የኢትዮጵያ የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ አገልግሎት በዲጂታል የታገዘ የትራፊክ አደጋ መረጃ አስተዳደር ሥርዓት ለኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አስረክቧል፡፡
የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርምን በላቀ የአመራር ጥበብ ለመፈፀም በትኩረት እየተሰራ ነው- አቶ አረጋ ከበደ
Jun 26, 2026 199
ባሕር ዳር፤ ሰኔ 19/2018(ኢዜአ)፡- በተቋማት እየተካሄደ የሚገኘውን የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም በላቀ የአመራር ጥበብ በመፈፀም የመልካም አስተዳደር ችግርን ለመቅረፍ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለፁ። በአማራ ክልል በመጀመሪያው ዙር ወደ መንግሥት አገልግሎት እና አሥተዳደር ሪፎርም የሚገቡ ተቋማትን የቅድመ ዝግጅት ሁኔታ በተመለከተ በባሕር ዳር ከተማ እየተገመገመ ነው። ርእሰ መስተዳድሩ አቶ አረጋ ከበደ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ መንግስት የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርምን በመቅረጽ የክልሉ ህዝብ የሚያነሳውን የመልካም አስተዳደር ችግር ለመቅረፍ እየሰራ ነው፡፡ በዚህም ለህዝቡ ፈጣን፣ ፍትሃዊና እርካታን የፈጠረ አገልግሎት ለመስጠት በቁርጠኝነት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥም በከተሞች መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግና በተቋማት የመንግስት አገልግሎት አስተዳደር ሪፎርምን በመተግበር ውጤታማ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በምክትል ርእሰ መስተዳድር ማእረግ የከተማ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የሪፎርሙ ስትሪንግ ኮሚቴ ሰብሳቢ አህመዲን መሃመድ (ዶ/ር) በበኩላቸው ሪፎርሙ የተቀናጀ መዋቅር፣ በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራርና ቁርጠኛ አመራርን የሚጠይቅ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ሪፎርሙን በክልል ደረጃ በተሟላ መልኩ በመተግበር ወደ ታች ለማውረድ እየተሰራ እንደሚገኝም ነው ያመለከቱት። የዛሬው መድረክ ዋና ዓላማም ቀድመው ሪፎርሙን ተግባራዊ ያደረጉ ተቋማት አተገባበር ያለበትን ሁኔታ በመገምገም በቀጣይ የላቀ አፈጻጸም ለማስመዝገብ ያለመ ነው ብለዋል። የአማራ ክልል የሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ባንችአምላክ ገብረማርያም እንደገለጹት፤ ባለፉት ሶስት ወራት በስምንት ተቋማት የተጀመረውን የሪፎርም ትግበራን ለማስፋት እየተሰራ ነው። ተቋማቱ በዝግጅት ምእራፍ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ማስፈጸሚያ መመሪያ በማዘጋጀትና የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት መስክ ያከናወኑት ተግባር አበረታች መሆኑን ገልጸዋል። ይህም ከሀምሌ ወር 2018 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ሪፎርም ትግበራው ለሚገቡ ተጨማሪ ዘጠኝ ተቋማት ልምድና ተሞክሮ ለማስተላለፍ እንደሚያስችል አስገንዝበዋል። በመጀመሪያው ምእራፍ የሪፎርም ትግበራ ግብርና ፣ ጤና ፣ ትምህርት፣ ስራና ክህሎት፣ ሲቪል ሰርቪስ ፣ ገንዘብ ፣ ገቢዎችና ፕላን ልማት ቢሮዎች መካተታቸው የሚታወስ ነው።
ማዕድን ዘርፍ- በሀገራዊ ለውጡ ያንሰራራው የኢትዮጵያ አቅም
Jun 26, 2026 258
በሙሴ መለሰ የኢትዮጵያ የማዕድን ዘርፍ በአገር በቀል የኢኮኖሚና የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎች ታግዞ፣ ባለፉት ዓመታት የታዩበትን የአሰራርና መዋቅራዊ ችግሮች በመቀረፍ ከፍተኛ የመነቃቃት ምዕራፍ ላይ ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአንድ ወቅት እንደገለጹት፣ ማዕድን በብዝኃ ዘርፍ የልማት ምልከታችን ውስጥ እና በአገሪቱ የሰላሳ ዓመታት የልማት ዕቅድ ውስጥ ትኩረት ከተሰጣቸው አምስት የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ ቁልፍ ዘርፍ ሆኖ ይቀጥላል። መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው የላቀ ትኩረትና ባከናወናቸው የማስተዋወቅ ሥራዎች፣ የማዕድን ልማት በአሁኑ ወቅት የሀገሪቱ የኢኮኖሚ ጀርባ አጥንት ወደ መሆን ተሸጋግሯል። ባለፉት ሦስት አሥርት ዓመታት ውስጥ የማዕድን ዘርፉ ለአጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) ያበረከተው አስተዋጽኦ ከዜሮ ነጥብ ስምንት በመቶ በታች የነበረ ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት ግን አስገራሚ መዋቅራዊ ሽግግር እየተመዘገበ ይገኛል። በቅርብ የወጡ የቁጥር መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፣ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያዎቹ ዘጠኝ ወራት ብቻ ዘርፉ ወደ አራት ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ ገቢ በማስመዝገብ የአገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ውስጥ ያለውን ድርሻ በከፍተኛ ሁኔታ አሳድጓል። ይህም ከቀዳሚው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ92 በመቶ የገቢ ዕድገትና የ27 በመቶ የምርት መጠን ብልጫ ማሳየቱን ያረጋግጣል። ምርቶቹ በከፍተኛ ደረጃ የሚላኩትም ወደ ሳውዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ አሜሪካ፣ ጀርመን እና ቻይና የመሳሰሉ ግዙፍ የዓለም ገበያዎች ነው። በዚህ ታሪካዊ ስኬት ውስጥ የወርቅ ምርት የወጪ ንግድ ዘርፉ ውስጥ በግንባር ቀደምትነት የሚመመዘገብ ማዕድን አይነት ነው። የወርቅ ወጪ ንግድ በያዝነው ዓመት ከአምስት ነጥብ አምስት ቢሊዮን ዶላር በላይ ያስገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ የማዕድን ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ይህም እንደ ከፍተኛ እምርታ ነው ማለት ይቻላል። በኢትዮጵያ ታሪክ ታይቶ በማይታወቅ መልኩ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያዎቹ ስምንት ወራት ብቻ 22 ነጥብ 5 ቶን ወርቅ ለውጭ ገበያ የቀረበ ሲሆን፣ እስከ ዓመቱ ማብቂያ ድረስ መጠኑ 32 ቶን ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል። በአሁኑ ወቅት የወርቅ ምርቱ 95 በመቶ የሚሆነው በባህላዊ አምራቾች ዘዴ የሚመረት ቢሆንም፣ ይህንን አሠራር ይበልጥ ዘመናዊና ውጤታማ ለማድረግ መንግሥት አነስተኛ የወርቅ ማጣሪያና ማቅለጫ ፋብሪካዎችን ለመገንባት በከፍተኛ ትኩረት እየሰራ ነው። የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት በጽኑ መሠረት ላይ ለማቆም ከውጭ የሚገቡ ስትራቴጂክ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት የመተካት ሰፊ ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛል። በዚህም መሠረት በየዓመቱ ለከሰል ምርት ግዢ ይወጣ የነበረውን 300 ሚሊዮን ዶላር ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ ምርት መተካት የተቻለ ሲሆን፣ የሲሚንቶ ምርትም ባለፉት ስምንት ዓመታት ከነበረበት ስምንት ሚሊዮን ቶን አሁን ላይ በዓመት ወደ 14 ሚሊዮን ቶን ምርቱ እንዲያድግ ተደርጓል። በተመሳሳይ መልኩ አገሪቱ በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የምታስገባውን የተፈጥሮ ጋዝ በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ በሀገር ውስጥ የማምረት እንቅስቃሴ ተጀምሯል። ይህም ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የጉባ ብስራቶች መካከል አንዱ ነው። ይህንን ተከትሎም በአዲስ አበባ-ጂቡቲ ኮሪደር ላይ ሦስት የጋዝ መሙያ ማደያዎች የተገነቡ ሲሆን፣ ከ1 ሺህ 500 በላይ የከተማ አውቶቡሶችን ከናፍጣ ነዳጅ ወደ ጋዝ የመቀየር የሽግግር ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ሚኒስቴሩ ገልጿል። በሌላ በኩል የብሔራዊ ኢኮኖሚው ምሰሶ የሆነውን የግብርና ዘርፍና የኢንዱስትሪ ግብዓቶችን ለማጠናከር ግዙፍ ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ወደ ሥራ ገብተዋል። ለ34 ሚሊዮን ያህል አርሶ አደሮች ፍላጎት ማሟያ በየዓመቱ ለማዳበሪያ ግዢ የሚወጣውን ሁለት ቢሊዮን ዶላር ለማስቀረት፣ መንግሥት የማዳበሪያ ፋብሪካ በሚቀጥሉት 29 እስከ 30 ወራት ውስጥ ተጠናቆ ወደ ሥራ እንዲገባ እየተሰራ ይገኛል። ይህም ሙሉ በሙሉ የሀገር ውስጥ ፍላጎትን የሚሸፍን ይሆናል። እንዲሁም በየዓመቱ የብረት ምርትን ከውጪ ለማስገባት የሚወጣውን አንድ ቢሊዮን ዶላር በሀገር ውስጥ ምርት ለመተካት የሚያስችል ግዙፍ የፋብሪካ ግንባታ ስምምነት ተፈርሞ ወደ ተግባር ተገብቷል። እንደሚታወቀው የለውጡ መንግስት ከመጣ በኋላ የፕሮጀክቶች መጀመር ብቻ ሳይሆን በተያዘላቸው ጊዜ ማጠናቀቅንም ቀድሞ ታሳቢ ያደርጋል። ለዚህ ደግሞ በቀደመው አሰራር የስምንት ሰዓት እለታዊ ስምሪት ሳይሆን 24 ሰዓታትን በመትጋት ማከናወን የሰርክ ተግባር ነው። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተከትሎ በሀገር ውስጥ እና በወጪ ገበያ ምርት መጠን ላይ ከፍተኛ እድገት እየተመዘገበ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት 10 ቢሊዮን ዶላር የሚገመቱ ግዙፍ ፕሮጀክቶች በማዕድን ዘርፉ ውስጥ ተሰማርተዋል። ይህም ከለውጡ በፊት ከነበረውና ከ100 ሚሊዮን ዶላር የማይበልጡ አነስተኛ ኢንቨስትመንቶች የነበሩበትን አሳሳቢ ሁኔታ በከፍተኛ ደረጃ የለወጠ ስኬት ነው። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ በዓለም ላይ ካሉ ያልተነኩ ግዙፍ የፖታሽ ክምችቶች መካከል አንዱ የሚገኝበትን የአፋር ክልል የማልማት ፈቃድ አግኝቶ ወደ ሥራ ገብቷል። ከዚህ ባለፈም ባለፉት 30 ዓመታት ምንም ዓይነት እሴት ሳይጨምርበት እንዲሁ ይላክ የነበረውን የታንታለም ማዕድን፣ አሁን ላይ በሀገር ውስጥ እሴት ጨምሮ ለዓለም ገበያ ለማቅረብ መንግስት ከአሜሪካ ኩባንያ ጋር ድርድር ላይ ይገኛል። ከወርቅ በተጨማሪ ለዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂና የባትሪ ምርት ወሳኝ የሆኑትን ሊቲየም፣ ኮባልትና ኒኬል የመሳሰሉ ማዕድናትን በስፋት ለማምረት ዝግጅቶች ተጠናቀዋል። የኢንቨስትመንት ምህዳሩን ይበልጥ ሳቢና ፍትሐዊ ለማድረግ የአሰራር ማሻሻያዎች ተተግብረዋል። የማዕድን ፍለጋ እና ምርት ፈቃድ አሰጣጥን ግልጽ ለማድረግ አሠራሩ ቅድሚያ የመጣን ቅድሚያ ማስተናገድ ላይ የተመሠረተ እንዲሆን ተደርጓል። የአገልግሎት አሰጣጡን ለማቀላጠፍም የወጪ ንግድ ኮንትራት ምዝገባ እና የመላኪያ ፈቃድ አገልግሎቶች ሙሉ በሙሉ ወደ ኦንላይን ሥርዓት የተሸጋገሩ ሲሆን፣ አዲስ ፈቃድ ለማውጣት ወይም ለማደስ የኤሌክትሮኒክስ የንግድ ሥርዓት ድረ-ገጽ እና የማዕድን ካዳስተር ሲስተምም ተዘርግቷል። በማዕድን ግብይት አዋጅ መሠረት በዘርፉ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች የማዕድን ላኪነት፣ የሀገር ውስጥ ንግድ፣ የማጣራትና ማቅለጥ እንዲሁም የአቅራቢነትና ዕደ-ጥበብ ፈቃዶች በግልጽና ቀልጣፋ በሆነ መንገድ እንዲሰጡ ተደርጓል። ከዚህ በተጨማሪም በማዕድን ማምረት ሥራዎች የሚገኘው ገቢ የተወሰነ ክፍል ማዕድኑ በሚወጣበት አካባቢ ለሚገኘው ማህበረሰብ ልማት እንዲውል በሕግ ተደንግጎ ወደ ሥራ መተርጎሙ የሕዝብን ተጠቃሚነትም አረጋግጧል። መንግሥት የኮንትሮባንድ ቁጥጥርን በከፍተኛ ደረጃ በማጥበቅና ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን በመቆጣጠር፣ ምርቶች በይፋዊ የገበያ ሰንሰለት ብቻ ለውጭ ገበያ እንዲቀርቡ በማድረግ ፈተናዎቹን በቁርጠኝነት እየመከተ ይገኛል። የማዕድን ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሃና ብርሃኑ ኢትዮጵያ ታከናውናለች በተሰኘው ብሔራዊ ጉባኤ ላይ እንደገለጹት፣ የመንግሥት ስልታዊ እቅድ እ.ኤ.አ. በ2030 የማዕድን ወጪ ንግድ ገቢን ከማዕድን ዘርፍ ከ10 ቢሊዮን ዶላር በላይ ማድረስ ነው። ይህ ታላቅ ራዕይ ኢትዮጵያን ከአፍሪካ አምስት ቀዳሚ የማዕድን አምራች ሀገራት ተርታ ለማሰለፍ ያለመም ነው። መንግስት በማዕድን ዘርፍ ያለውን ይህንን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ በመጠቀም ወደ ላቀ ብልፅግና ለመቀየር በዘርፉ ለሚሰማሩ የሀገር ውስጥና የውጭ ኢንቨስተሮች ሁሉን አቀፍ ድጋፍና ማበረታቻ ለማድረግ ሙሉ በሙሉ ዝግጁ መሆኑን አረጋግጧል።
ከአፍሪካ ትልሞች ጋር የተሳሰረው የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት
Jun 26, 2026 270
ኢትዮጵያ በታሪክ አጋጣሚዎች በአፍሪካ የነጻነት ትግል ግንባር ቀደም በመሆን፣ የቅኝ ግዛት ቀንበርን በመስበር ለቀሪው አህጉር የተስፋ ብርሃን የፈነጠቀች ሀገር ናት። ዛሬም፣ኢትዮጵያ ይህንን ታሪካዊ አደራ በመቀጠል፣ በሜጋ ፕሮጀክቶቿ ስኬት የአፍሪካን የኢኮኖሚ ነጻነትና ትስስር በመምራት ላይ ትገኛለች።እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ፣ የቢሾፍቱ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ የጎዴ የዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካ፣የኦጋዴን ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ ፕሮጀክት እንዲሁም በሌሎች ዘርፎችም ጭምር ከሀገር ስኬት ባሻገር የአህጉሪቱን የልማት ህልም እውን የሚያደርጉ ቁልፍ መሰረተ ልማቶች በመከወን ላይናቸው። የአፍሪካ የኢኮኖሚ ዕድገት ዋነኛው ማነቆ የኃይል አቅርቦት እጥረት መሆኑ አጠያያቂ አይደለም።ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ፍላጎት ማሟያ ብቻ ሳይሆን፣ለቀጠናው አገራት አስተማማኝ የኃይል ምንጭ በመሆን የአፍሪካን የኢንዱስትሪ ሽግግር የሚያፋጥን የኃይል ማዕከል በመሆን ለቀጣናው የቀረበ ውድ ስጦታ ነው። ይህ ፕሮጀክት አፍሪካ በራሷ ሃብት ተጠቅማ የኃይል ዋስትናዋን ማረጋገጥ እንደምትችል የሚያሳይ በራስ የመተማመን ምልክት ነው። ኢትዮጵያ በሜጋ ፕሮጀክቶቿ የምትገነባው የሎጂስቲክስ አውታርም፣ ለአፍሪካ የንግድ ትስስር እውን መሆን ወሳኝ ነው።የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ለቀጣዩ የአህጉሪቱ የዕድገት ምዕራፍ የተዘጋጀ ስልታዊ ምላሽ ከመሆኑም በላይ፣ የኢትዮጵያን ብልጽግና ከአፍሪካ ብልጽግና ጋር የሚያቆራኝ ወሳኝ የሜጋ ፕሮጀክት ነው። አፍሪካ በራሷ ጥረት የዓለም አቀፍ ደረጃ መሰረተ ልማቶችን መገንባት እንደምትችል ኢትዮጵያ በእዚህ ፕሮጀክቷ በኩል መልዕክት እያስተላለፈች ነው።ይህ አውሮፕላን ማረፊያ ኢትዮጵያን በአህጉሪቱ የልማት ግንባር ቀደምትነቷን የሚያጸና፣ እንዲሁም የነገውን የአፍሪካ ህልም ወደ ተግባር የሚቀይር የልህቀት ማማ ነው። የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት ከአፍሪካ የልማት ትልም ጋር የተሳሰረበት ሌላው ቁልፍ ምክንያት አፍሪካ ያለ ውጭ ዕርዳታና ጣልቃ ገብነት፣በራሷ ህዝብ ሃብትና ጥረት ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መገንባት እንደምትችል ኢትዮጵያ በተግባር እያሳየች ነው።ይህ ለሌሎች የአፍሪካ አገራት ታላቅ የልማት ተምሳሌት ነው። የቴክኖሎጂ ሽግግርን፣የባለሙያ አቅም ግንባታን እንዲሁም የፕሮጀክት አመራር ክህሎትን በማጎልበት፣ኢትዮጵያ የአፍሪካን የሰው ሃይል ለለውጥ እያዘጋጀች ስለመሆኑ አያጠራጥርም። የሜጋ ፕሮጀክቶቹ ተፅዕኖ ከኢትዮጵያ ድንበር አልፎ በምስራቅ አፍሪካ ቀጠና ላይ ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ነው።ቀጠናዊ የኃይል አቅርቦት፣የንግድ መስመሮች፣ እንዲሁም የኢንዱስትሪ መዳረሻዎች መፈጠር፣ ለጎረቤት አገራት የኢኮኖሚ እድገት የጋራ ማጠንጠኛ ሆነዋል። ኢትዮጵያ የምትከተለው የልማት ጎዳና ከድህነት እና ከግጭት ወጥመድ በማውጣት፣ ወደ የጋራ ብልጽግና የሚያመራውን የአፍሪካ ህብረት የ2063 ራዕይ እያሳካ ይገኛል። ኢትዮጵያ በታሪክ አፍሪካ ነጻነቷን እንድታውጅ ከፊት ሆና እንደመራችው ሁሉ፣ ዛሬም በሜጋ ፕሮጀክቶቿ አማካኝነት አፍሪካ ከድህነት ተላቃ የኢኮኖሚ ነጻነቷን እንድታረጋግጥ መሪ ፊታውራሪ ሆናለች። እነዚህ ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆኑ፣የአፍሪካ የኩራት ምንጭና የህልውና መሰረቶች ናቸው።ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለው የልማት እንቅስቃሴ፣ አፍሪካ በራሷ መንገድ የራሷን የልማት ታሪክ እየጻፈች መሆኗን የሚያረጋግጥ ነው። በመሆኑም የኢትዮጵያ ሜጋ ፕሮጀክቶች ስኬት፣የነገዋ አፍሪካ በዓለም መድረክ ያላት ተጽዕኖ መገለጫ፣ እንዲሁም የጋራ የወደፊት ብልጽግናዋ ዋስትና ናቸው።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በተያዘው የመኸር ወቅት 31 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ ይለማል
Jun 26, 2026 201
አምቦ ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ ዞን በተያዘው የመኸር እርሻ 31 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ የማልማት ስራ መጀመሩን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። የክልል፣ የዞን እና የወረዳ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በዞኑ ኢሉ ገላን ወረዳ የ2018/19 የምርት ዘመን ሩዝን በኩታ ገጠም የማልማት ስራ ተጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ ላይ የተገኙት የምዕራብ ሸዋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ እንደገለጹት፤ በክልሉ መንግሥት በግብርናው ዘርፍ ተቀርጾ ወደ ስራ ከገቡት 33 ኢኒሼቲቮች መካከል የሩዝ ምርት አንዱ ነው። የሩዝ ምርት በዞኑ በስፋት ያልተለመደ ቢሆንም፣ ከጥቂት ዓመታት ወዲህ መንግሥት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ህብረተሰቡ በአንድነት በኩታ ገጠም ተደራጅቶ ወደ ስራው መግባቱን ጠቅሰዋል። ዘርፉ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ማሳደግ የሚችል በመሆኑ፣ በ36 ሄክታር መሬት ላይ የሩዝ ዘር መዘራት መጀመሩን ገልጸዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብዲሳ ሀይሉ በበኩላቸው በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል አይነቶች ለመሸፈን ታቅዷል ብለዋል። ከዚህ ውስጥ ከ31 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነውን መሬት በሩዝ ምርት ለመሸፈን ታቅዶ ስራው ተጀምሯል ብለዋል። የኢሉ ገላን ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርናና መሬት አስተዳደር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ በንቲ በበኩላቸው፣ የወረዳው አርሶ አደሮች የሩዝ ምርት የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴን እየተላመዱ መምጣታቸውን ገልጸዋል። በወረዳው በ2018/19 የምርት ዘመን 5 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ ምርት ለመሸፈን ታቅዶ፣ የግብርና ግብዓቶችን ለአርሶ አደሮቹ በማቅረብ ዘር የመዝራት ስራ መጀመሩን ጠቁመዋል። ከወረዳው አርሶ አደሮች መካከል ዘውዱ ዘነበ፤ የሩዝ ሰብልን በኩታ ገጠም መዝራት ከጀመሩ አራት ዓመታት እንደሆናቸው ገልጸው፣ ቀደም ሲል ከሄክታር አነስተኛ ምርት ያገኙ እንደነበር አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት ግን በግብርና ባለሙያዎች በሚደረግላቸው ሙያዊ ድጋፍ ታግዘው ከአንድ ሄክታር ማሳቸው እስከ 80 ኩንታል የሩዝ ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውን ተናግረዋል።
ሀገር አቀፍ የህብረት ሥራ ስትራቴጂ እና ፍኖተ ካርታ የማህበራትን አሠራር ዘመናዊ በማድረግ ወደ አዲስ ምዕራፍ የሚያሸጋግር ነው
Jun 26, 2026 281
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ አዲሱ ሀገር አቀፍ የህብረት ሥራ ስትራቴጂ እና ፍኖተ ካርታ የህብረት ሥራ ማህበራትን አሠራር ዘመናዊ በማድረግ ወደ አዲስ ምዕራፍ የሚያሸጋግር መሆኑን የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ። የግብርና ሚኒስቴር የአስር ዓመት ሀገር አቀፍ የህብረት ሥራ ስትራቴጂ እና ፍኖተ ካርታ የንቅናቄ መድረክ ማካሄድ ጀምሯል። የግብርና ሚኒስትሩ አዲሱ አረጋ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ አዲሱ ፍኖተ ካርታ የህብረት ሥራ ማህበራትን አሠራር ዘመናዊ በማድረግ ወደ አዲስ ምዕራፍ የሚያሸጋግር ነው። ማህበራቱን በስፋት በማደራጀትና ተወዳዳሪነታቸውን በማሳደግ የገጠርና የከተማ ትስስርን ማጠናከር እንደሚቻል ገልጸው፣ ይህም ኢትዮጵያ የጀመረችውን የብልፅግና ጉዞ ለማረጋገጥ ትልቅ አቅም እንደሚሆን ጠቁመዋል። ስትራቴጂውና ፍኖተ ካርታው በዋናነት በርካታ ጠቀሜታዎችን እንደሚያስገኝ ጠቁመው የግብርና ሽግግርን በማፋጠን፣ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩንና የአርብቶ አደሩን የኑሮ ደረጃ ከፍ ያደርጋል ብለዋል። በተጨማሪም የህብረት ሥራ ማህበራትን የሚያዘምን መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፤ የህብረት ሥራን ማዘመን ግብርናን ማዘመን ነው፤ግብርናን ማዘመን ደግሞ የሀገርን ኢኮኖሚ ማረጋገጥ ነው ሲሉ አስገንዝበዋል። ከዚህ ቀደም በህብረት ሥራ ማህበራት ውስጥ ሲያጋጥሙ የነበሩ መዋቅራዊና አሠራራዊ ተግዳሮቶችን በመቅረፍ ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆኑ ያስችላልም ብለዋል፡፡ ስትራቴጂው ሙሉ በሙሉ ወደ ተግባር ሲገባ ምርትና ምርታማነትን በማረጋገጥ ከሀገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሪ እንደሚያስገኝም ጠቁመዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ዕድገት ከፍ የሚያድርግ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ይህ አገር አቀፍ የአስር ዓመት ስትራቴጂና ፍኖተ ካርታ የግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚን በማፋጠን፣ ማህበራቱ በሀገር ውስጥ ምርት ሥርጭትና በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ያላቸውን ተሳትፎ የጎላ እንደሚያደርገው በንቅናቄ መድረኩ ላይ ተመልክቷል።
በከተማው የተመዘገቡ ዘርፈ ብዙ ለውጦች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የበኩላችንን እንወጣለን
Jun 26, 2026 134
ዲላ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦ በከተማው የተመዘገቡ ዘርፈ ብዙ ለውጦች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የበኩላችንን እንወጣለን ሲሉ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የዲላ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ይፋ ባደረገው መሰረት በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ብልጽግና ፓርቲ አብላጫ የምክር ቤት ወንበር በማግኘት መንግሥት ለመመስረት የሚያስችለውን ድምጽ አግኝቷል። ለኢዜአ አስተያየታቸው የሰጡ የዲላ ከተማ ነዋሪዎች በለውጡ መንግሥት በከተማው የተመዘገቡ ዘርፈ ብዙ ለውጦች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የበኩላችንን እንወጣለን ብለዋል፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል መምህር ዮናስ ታደለ እንደተናገሩት፤ በከተሞች መሰረተ ልማትና በኮሪደር ልማት የተከናወኑ ተግባራት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ናቸው ብለዋል። እንዲሁም ህብረተሰቡን በማስተባበር የትምህርት ቤቶችን ደረጃ ለማሻሻል የተደረጉ ጥረቶች ብቁና ተወዳዳሪ ዜጋ ለማፍራት የሚደረገውን ጉዞ የሚያግዙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በከተማው የተመዘገበው ዘርፈ ብዙ ለውጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በምርጫ ያሸነፈው ብልጽግና ፓርቲ ከሚመሰርተው መንግሥት ጎን በመሰለፍ የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል። ነጻ፣ ገለልተኛና አሳታፊ በሆነ ምርጫ አሸናፊው ፓርቲ መታወቁ የዲሞክራሲ ባህል እየጎለበተ መምጣቱን የሚያመላክት መሆኑን ያነሱት ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ ተስፋነሽ ኢሳያስ ናቸው። በተለይ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ሂደት ለዴሞክራሲ ባህል ግንባታ መሰረት የሚጥል ነው ብለዋል፡፡ በከተማው የታየው ለውጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ከአሸናፊ ፓርቲው ጋር በቅንጅት ለመስራት ዝግጁ መሆናቸውንም አረጋግጠዋል። በዲላ ዩኒቨርሲቲ የታሪክና ቅርስ አስተዳደር መምህርና ተመራማሪ ሰረቀብርሃን ለገሰ በበኩላቸው፤ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ከዝግጅት እስከ ውጤት ገለልተኝነትና አሳታፊነት በተጨባጭ የተረጋገጠበት ነው ብለዋል። በዴሞክራሲያዊ መንገድ ወደ ስልጣን የመጣ መንግሥት ለህዝብ የልማት ጥያቄ ምላሽ ከመስጠት አንጻር የተሻለ መሆኑን አንስተው አዲሱ መንግሥት የልማት ውጥኑን ከዳር እንዲያደርስ የበኩላቸውን እንደሚወጡም ተናግረዋል።
በዞኑ የሰፈነው ሰላም የነዋሪውን የመሠረተ ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ አስችሏል
Jun 26, 2026 166
ጊምቢ፤ ሰኔ 19/2018 (ኢዜአ)፦በምዕራብ ወለጋ ዞን የሰፈነው ሰላም የነዋሪውን የመሠረተ ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ አስችሏል ሲሉ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ገለጹ። የዞኑ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በዞኑ የተለያዩ ወረዳዎች በበጀት ዓመቱ ግንባታቸው የተጠናቀቀ የመሠረተ ልማት ተቋማትን በማስመረቅ ላይ ይገኛሉ። በዚሁ መሠረት በዞኑ ቆንዳላ ወረዳ ከ219 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነባው የንጹሕ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት የተመረቀ ሲሆን፣ በመንዲ ከተማ አስተዳደር ደግሞ በ42 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባ የአስተዳደር ሕንጻ ለአገልግሎት በቅቷል። በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ተሊላ ተረፈ እንደተናገሩት፤ በበጀት ዓመቱ በዞኑ የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው የጊዜ ገደብና ጥራት ተጠናቅቀው ለአገልግሎት እየበቁ ነው። ከእነዚህ የመሠረተ ልማት ተቋማት መካከል በቆንዳላ ወረዳ ለአገልግሎት የበቃው የንጹሕ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት የነዋሪው የረጅም ጊዜ ጥያቄ እንደነበረ ገልጸዋል። በአካባቢው የነበረው የጸጥታ ችግር መፍትሄ አግኝቶ አስተማማኝ ሰላም በመስፈኑ፣ የመሠረተ ልማት ተቋማቱን ግንባታ ለማፋጠን ትልቅ ዕድል መፍጠሩን አስረድተዋል። በቀጣይም የተጀመሩ የልማት ሥራዎች የበለጠ እንዲጠናከሩ ሕዝቡ ከምንጊዜውም በላይ የአካባቢውን ሰላም በንቃት መጠበቅ እንዳለበት አሳስበዋል። የዞኑን የሕዝብ የልማት ጥያቄዎች በሂደት በመመለስ፣ የአካባቢውን የልማት አቅም አሟጦ ለመጠቀም እንደሚሠራም አስረድተዋል። በሕዝቡና በመንግሥት በጀት የተገነቡ ፕሮጀክቶች ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ አስፈላጊው ጥበቃና እንክብካቤ ሊደረግላቸው እንደሚገባም ጠቅሰዋል። የምዕራብ ወለጋ ዞን ውኃና ኢነርጂ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሰለሞን ቀነኒ በበኩላቸው፤ በበጀት ዓመቱ የንጹሕ መጠጥ ውኃ አቅርቦትን የሚያሳድጉ የውኃ ፕሮጀክቶች ግንባታ ሲካሄድ መቆየቱን ተናግረዋል። እነዚህ የንጹሕ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክቶች የ116 ሺህ ሰዎችን የንጹሕ መጠጥ ውኃ ችግር ለመፍታት የሚያስችሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል። በተመሳሳይም የመንዲ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ፈቀደ ታሲሳ፣ በከተማው ለአገልግሎት የበቃው የአስተዳደር ሕንፃው በከተማው ውስጥ የተሳለጠና የተቀናጀ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጠት ያስችላል ብለዋል። ሕንጻው 370 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ፣ 28 የተለያዩ የአገልግሎት ክፍሎች ያሉትና በአንድ ጊዜ በርካታ ተገልጋዮችን ማስተናገድ የሚችል መሆኑን ገልጸዋል። ከቆንዳላ ወረዳ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ሙፍተሃ የሱፍ በሰጡት አስተያየት፤ ፕሮጀክቱ የረጅም ጊዜ የንጹሕ መጠጥ ውኃ አቅርቦት ችግራቸውን እንደሚያቃልልላቸው ተናግረዋል። በአካባቢው ንጹሕ የመጠጥ ውኃ ለማግኘት ረጅም ርቀት በእግር መጓዝ ግዴታቸው እንደነበር አስታውሰው፣ ከዚህ ቀደም በነበረው የንጹሕ ውኃ አቅርቦት እጥረት ሳቢያ ለተለያዩ የውኃ ወለድ በሽታዎች ተጋልጠው መቆየታቸውንም ገልጸዋል። ሌላኛዋ የወረዳው ነዋሪ ወይዘሮ ሾኔ ሻፊ በበኩላቸው፤ አሁን ላይ ጥያቄያቸው ምላሽ በማግኘቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል። መንግሥት የሕዝቡን የመሠረተ ልማት ፍላጎት ጥያቄዎች ለመመለስ እያደረገ ያለውን ጥረት ያደነቁት ነዋሪዋ፤ ለአገልግሎት የበቃው ይህ የንጹሕ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት ረጅም ዕድሜ እንዲያገለግል ተገቢውን ጥበቃና እንክብካቤ በማድረግ የበኩላቸውን ድርሻ እንደሚወጡም አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያና ዩናይትድ ኪንግደም ታሪካዊ ግንኙነት ወደላቀ ስትራቴጂክ አጋርነት እየተሸጋገረ ነው
Jun 25, 2026 611
አዲስ አበባ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያና ዩናይትድ ኪንግደም ታሪካዊ ግንኙነት ወደላቀ ስትራቴጂክ የዲፕሎማሲ አጋርነት እየተሸጋገረ መሆኑን በዩናይትድ ኪንግደም የኢትዮጵያ አምባሳደር ብሩክ መኮንን ገለጹ። በኢትዮጵያ እና እንግሊዝ መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ትብብር ለማሳደግ የተዘጋጀው የኢትዮ-እንግሊዝ የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረም 2026 በለንደን ከተማ ተካሂዷል። በዩናይትድ-ኪንግደም የኢትዮጵያ አምባሳደር ብሩክ መኮንን በዚሁ ጊዜ፤ ኢትዮጵያና እንግሊዝ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ዘመናትን የተሻገር ታሪካዊ ግንኙነት ያላቸው ወዳጅ ሀገራት ናቸው ብለዋል። የሀገራቱ መልካም ግንኙነትም የንግድና ኢንቨስትመንት የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ትብብርን በማሳደግ የህዝብ ለህዝብ ትስስርን ጭምር እያጠናከረ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅትም የኢትዮጵያና ዩናይትድ ኪንግደም ታሪካዊ ግንኙነት ወደላቀ ስትራቴጂክ የዲፕሎማሲ አጋርነት እየተሸጋገረ መሆኑን ተናግረዋል። የሀገራቱ የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረምም የኢኮኖሚክ ዲፕሎማሲ አጋርነትን ለማጎልበት ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የብዝኅ ዘርፍ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ ለሀገራቱ ሁለንተናዊ የዲፕሎማሲ ትብብር አስቻይ ሁኔታ መፍጠሩንም አንስተዋል። በቀጣይም የሀገራቱን ሁለንተናዊ የዲፕሎማሲ ትብብር የበለጠ በማጠናከር የጋራ ተጠቃሚነትን ለማሻሻል በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በዩናይትድ ኪንግደም የኢትዮጵያ ኤምባሲም የሁለቱን ሀገራት የንግድ፣ የኢንቨስትመንትን፣ የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ትብብር ወደ ላቀ ስትራቴጂክ አጋርነት ለማሸጋገር በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በፎረሙ ላይ የሀገራቱ የፖሊሲ አውጪ ሙያተኞች፣ ባለሃብቶችና የተለያዩ ተቋማት ጋር የሃሳብ ልውውጦች መደረጋቸው ተመላክቷል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች የሚመልሱ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቁ
Jun 25, 2026 467
አምቦ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን የቆዩ የልማት ጥያቄዎች ለመፍታት የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት አውታሮች በሁለት ዙር ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በዞኑ ኢሉ ገላን ወረዳ ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁት ኮሪደር ልማት፣ የእንስሳት ጤና ኬላ፣ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት እና ሌሎች የመሰረተ ልማት ተቋማትም ይገኙበታል። በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የምዕራብ ሸዋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ እንደገለጹት፤ በዞኑ በሕዝብና በመንግሥት ትብብር የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት እየበቁ ነው። በበጀት ዓመቱ በመጀመሪያው ዙር 391 የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው አገልግሎት መጀመራቸውን የገለጹት አስተዳዳሪው፤ የሁለተኛው ዙር ምረቃ በኢሉ ገላን ወረዳ መጀመሩን ጠቁመዋል። ግንባታቸው ተጠናቆ ምርቃታቸው የተጀመረው የሁለተኛ ዙር ፕሮጀክቶች ቁጥር 128 መሆኑንም ገልጸዋል። የኢሉ ገላን ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አሚን ነሻ በበኩላቸው፤ በወረዳው በመንግሥት በጀትና በሕብረተሰቡ ተሳትፎ ከ106 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 18 የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን አስታውቀዋል። የተገነቡት መሰረተ ልማቶች የአካባቢውን ሕብረተሰብ ዘመናት ያስቆጠሩ ጥያቄዎች የሚፈቱ መሆናቸውን የገለጹት የወረዳው አስተዳዳሪ፤ ሕዝቡ ለፕሮጀክቶቹ አስፈላጊውን እንክብካቤ በማድረግ ለመጪው ትውልድ ማስተላለፍ እንዳለበት አሳስበዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢሉ ገላን ወረዳ ነዋሪዎችም በአካባቢያቸው ለአገልግሎት የበቁ ፕሮጀክቶች የረጅም ጊዜ ጥያቄያቸውን ከመመለስ ባለፈ፣ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያሳድጉት ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። አቶ ሁንዱማ ታረሳ "በቀበሌያችን የተገነባው ዲጂታል ቤተ መጻሕፍት አገልግሎት መጀመሩ የአካባቢው ተማሪዎች በቴክኖሎጂ ታግዘው ዕውቀት እንዲቀስሙና በሀገር አቀፍም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ትልቅ እገዛ ያደርጋል" ብለዋል። ወጣት ደራርቱ ወጋሪ በበኩሏ፤ ለአገልግሎት የበቁት መሰረተ ልማቶች የአካባቢውን ሕብረተሰብ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ከመሆናቸውም በላይ፣ ለወጣቶች ሰፊ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ በመሆናቸው ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ገልጻለች።
የሀረር ፌዴራል ፖሊስ ሆስፒታል ማስፋፊያ የክልሉን የሜዲካል ቱሪዝም የሚያጎለብት ነው
Jun 25, 2026 260
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 18/2018/(ኢዜአ) ፦ የሀረር ፌዴራል ፖሊስ ሆስፒታል ማስፋፊያ ፕሮጀክት የክልሉን የሜዲካል ቱሪዝም ይበልጥ የሚያጎለብት ነው ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ገለፁ። ርዕሰ መስተዳድሩ የሀረር ፌዴራል ፖሊስ ሆስፒታል ማስፋፊያ የግንባታን የአፈጻጸም ሂደት ተመልክተዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በጉብኝታቸው የሪፈራል ሆስፒታሉን ግንባታ በተያዘለት የጊዜ ገደብ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ስለመሆኑ ማየታቸውን ገልጸዋል። የሆስፒታሉ ማስፋፊያ ግንባታ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ሲጀምርም የህክምና አገልግሎቱን ወደ ተሻለ ደረጃ የሚያደርስ መሆኑን ነው የተናገሩት። በክልሉ ለጤና አገልግሎት ተደራሽነት ልዩ ትኩረት ተሰቶት ወደ ስራ መገባቱን የጠቆሙት ርዕሰ መስተዳድሩ የሆስፒታሉ ማስፋፊያም በክልሉ በጤና ዘርፍ የሚሰጠውን አገልግሎት ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የራሱን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ገልፀዋል። በተለይ ሀረር ጎረቤት አገራትን ጨምሮ ከአጎራባች ክልሎች ለህክምና የሚመጡ በርካታ ተገልጋዮች የሚስተናገዱባት የሜዲካል ቱሪዝም ከተማ መሆኗን ጠቅሰው የሆስፒታሉ ማስፋፊያ የሜዲካል ቱሪዝሙን ይበልጥ የሚያጎለብት ነው ብለዋል። የማስፋፊያ ፕሮጀክቱ ጥሩ በሚባል አፈፃፀም ላይ እንደሚገኝ በማመላከት በፍጥነት ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት እንዲችል የክልሉ መንግስት ድጋፍ እንደሚያደርግም ርዕሰ መስተዳድሩ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ እመርታ ለውጭ አልሚ ባለሃብቶች ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳርን ፈጥሯል
Jun 25, 2026 242
አዲስ አበባ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ልማት እመርታ ለውጭ አልሚ ባለሃብቶች ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳር መፍጠሩን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ ገለጹ። በኢትዮጵያ እና ዩናይትድ ኪንግደም መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ትብብርን ለማሳደግ የተዘጋጀው የኢትዮ-እንግሊዝ የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረም 2026 በለንደን ከተማ ተካሂዷል። የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ አምራች የሰው ኃይል፣በዓመት ከሶስት ጊዜ በላይ የሚያመርት መሬትና የብዝኅ ጸጋ ምድር ናት ብለዋል። በሀገራዊ ለውጡ ማግስት ተግባራዊ የተደረገው የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ የልማት አቅጣጫም በግብርና፣ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ቱሪዝምና ዲጂታል ኢኮኖሚ ዘርፎች ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚም በሁሉም ወቅቶች ዘመናዊ አስተራረስ ምኅዳርን በማስፋት የኢንዱስትሪ ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የኢትዮጵያን የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢ ለማሻሻል ተግባራዊ የሆኑ የሕግና የአሰራር ማሻሻያዎችም ለውጭ ባለኃብቶች አስቻይ ምኅዳር መፍጠሩን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የግብርና ምርታማነት አቅም የምግብ ሉዓላዊነትን በሚያረጋግጥ ትክክለኛ አቅጣጫ ላይ እየተመራ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል። የእንግሊዝ አልሚ ባለሃብቶችም የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ አስቻይ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳር መጠቀም የሚችሉበት ዕድል መፈጠሩንም አብራርተዋል።
የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው የተረጋጋ፣ተገማችና ተወዳዳሪ የንግድና ኢንቨስትመንት ሥነ ምህዳር ፈጥሯል
Jun 25, 2026 475
አዲስ አበባ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው የተረጋጋ፣ ተገማችና ተወዳዳሪ የንግድና ኢንቨስትመንት ሥነ ምህዳር መፍጠሩን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያና እንግሊዝ መካከል ያለውን ሁሉን አቀፍ ትብብር ይበልጥ ለማሳደግ የተዘጋጀው የ“እንግሊዝ-ኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረም 2026” በለንደን ተካሂዷል። በፎረሙ ላይ የተገኙት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ምንዛሪ ግኝትን በማሳደግ ረገድ ተስፋ ሰጭ ውጤት ያስመዘገበ ሲሆን፣የተረጋጋ፣ ተገማችና ተወዳዳሪ የንግድና ኢንቨስትመንት ሥነ ምህዳር መፍጠር ችሏል። ኢትዮጵያና እንግሊዝ ከረጅም ጊዜ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ባሻገር ጥልቅና ሁሉን አቀፍ የትብብር ታሪክ ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅትም በንግድ፣በልማት አጋርነት፣ በኢንቨስትመንት መስፋፋት እንዲሁም በማደግ ላይ ባለው የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ አማካኝነት የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ይበልጥ እየተጠናከረ መምጣቱን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ወሳኝ በሆነ የኢኮኖሚ ሽግግር ምዕራፍ ላይ እንደምትገኝ የጠቆሙት ሚኒስትሩ፥የዚህ ሽግግር ስኬት እውን ሊሆን የሚችለው በጠንካራና ተለዋዋጭ የሕዝብና የግል አጋርነት እንዲሁም በግሉ ዘርፍ ንቁ ተሳትፎ መሆኑን ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2019 የጀመረችውን የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀምሌ 2024 ወደ ላቀ ደረጃ በማሸጋገር የውጭ ምንዛሪ ተመን በገበያ እንዲወሰን ማድረጓን አስታውሰዋል። ከዚህም በተጨማሪ ዘመናዊ የገንዘብ ፖሊሲና ጠንካራ የታክስ አስተዳደር ስርዓት መዘርጋቱን ጠቅሰው፣ የመንግስት የልማት ድርጅቶች ሪፎርም ተደርገው ቁልፍ የኢኮኖሚ ዘርፎች ለግሉ ዘርፍ ክፍት ሆነዋል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም ከጥቂት ዓመታት በፊት ለውጭ አልሚዎች ትልቅ ፈተና የነበረው የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ችግር በሪፎርሙ አማካኝነት ሊፈታ መቻሉንም አረጋግጠዋል፡፡ ይህ ማክሮ-ኢኮኖሚያዊ ሪፎርም በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጨባጭና ገንቢ ውጤቶችን ማስመዝገቡንም አብራርተዋል፡፡ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚው ሪፎርም የሀገር ውስጥ ገቢ በ61 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን ጠቅሰዋል፡፡ ወደ ውጭ የሚላከው የምርት መጠን በ119 በመቶ እድገት ማስመዝገቡንም ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከ120 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ያላት፣ በአፍሪካ ትልቁ ገበያና እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ባለቤት መሆኗን ያነሱት ሚኒስትሩ፤ የውጭ ባለሀብቶች በተለያዩ ዘርፎች ላይ እንዲሰማሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ግብርና የሀገሪቱን ጥቅል ሀገራዊ ምርት (GDP) 40 በመቶ የሚሸፍን፣ 80 በመቶ የሚሆነውን የውጭ ምንዛሪ ገቢ የሚያስገኝና 75 በመቶ የሥራ ዕድል የፈጠረ የኢኮኖሚው ምሰሶ ነው ብለዋል፡፡ የውጭ ባለሀብቶች በዘመናዊ ግብርና፣በግብርና ምርቶች ማቀነባበርና እሴት መጨመር ላይ በስፋት በመሰማራት ውጤታማ መሆን እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡ ሀገሪቱ የአምራች ኢንዱስትሪውን ምርታማነት ለማሳደግ፣ ለተኪ ምርቶች ትኩረት ለመስጠትና ከዓለም አቀፍ የእሴት ሰንሰለት ጋር ለመቀላቀል ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ “የኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ በስፋት እየተተገበረ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡ ወርቅን ጨምሮ ሌሎች ወሳኝና ስትራቴጂካዊ ማዕድናት መገኛ በሆነችው ኢትዮጵያ ውስጥ በዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ የሪፎርም ተግባራት በርካታ የውጭ ኢንቨስተሮችን እየሳቡ እንደሚገኙም ጠቁመዋል፡፡ የኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት ሁኔታ ከበፊቱ ሙሉ በሙሉ መቀየሩን ጠቁመው፤ የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን በማስፋፋትና ተቋማትን በማጠናከር እጅግ ምቹ የኢንቨስትመንት ከባቢ መፈጠሩን ገልጸዋል። የሪፎርም አጀንዳው ዋነኛ ትኩረት ተቋማትን ማጠናከር እንደሆነና ይህም የዓለም የንግድ ድርጅት አባልነትን ጨምሮ ከዓለም አቀፍ ደረጃዎች ጋር የተጣጣመና የኢንቨስተሮችን መብትና ፍላጎት ማዕከል ያደረገ መሆኑን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የግሉን ኢንቨስትመንት እንደ ረጅም ጊዜ የልማት አጋር እንደምትመለከት የገለጹት ሚኒስትሩ፤ የእንግሊዝ ባለሀብቶችና የንግዱ ማህበረሰብ በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች እንዲሰማሩ በሯ ክፍት መሆኑን በማረጋገጥ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
ኢትዮጵያ ታከናውናለች፡ በግብርናው ዘርፍ የተመዘገቡ ሁለንተናዊ ስኬቶችና መዋቅራዊ ሽግግሮች
Jun 25, 2026 225
በለውጡ ዓመታት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት በሆነው በግብርናው ዘርፍ ላይ የተከናወኑት ሁለንተናዊ የፖሊሲ ማሻሻያዎች በዘርፉ ተጨባጭ የሆነ መዋቅራዊ ሽግግር እንዲመዘገብ አድርጓል። መንግሥት ለዘርፉ የሰጠው ልዩ ትኩረትና የተቀረጹ ስትራቴጂካዊ ስልቶች፣ ግብርናውን በአንድ ወጥ ሰብል (Monoculture) እና በዝናብ ላይ ብቻ ከተመሰረተ አካሄድ በማውጣት፣ ወደ ተደራጀ፣ ምርታማና የብዝሃ-ሕይወት አቅምን ወደሚያሳድግ ዘመናዊ የኢኮኖሚ ምሰሶነት ቀይረውታል። ይህ ስኬት ጥቂት ዘርፎች ላይ ብቻ ሳይሆን በሰብል ልማት፣ በእንስሳት ሀብት፣ በሆርቲካልቸር፣ በደንና ተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ፣ በሜካናይዜሽን እንዲሁም በገበያና አግሮ-ኢንዱስትሪ ትስስር ዙሪያ ሰፊ ውጤቶችን አምጥቷል። በሰብል ልማት ረገድ የተመዘገበው ታሪካዊ ስኬት በበጋ መስኖ ስንዴ አብዮት የሚገለጽ ሲሆን፣ ዝናብን ብቻ የመጠበቅን ልማድ በመስበርና ሰፊ የመስኖ መሠረተ-ልማትን በመጠቀም ኢትይጵያ ለአገር ውስጥ ፍጆታ የምታደርገውን የከፍተኛ ስንዴ ግዢ በማስቀረት ራሷን ችላለች። ከዚህም ባለፈ፣ የተረፈውን ምርት ወደ ውጭ ሀገራት መላክ የተጀመረበት አዲስ ታሪካዊ ምዕራፍ የተፈጠረ ሲሆን፣ ከስንዴ በተጨማሪም እንደ አኩሪ አተር፣ ሰሊጥ ያሉ የቅባትና ጥራጥሬ እህሎች ምርታማነት በክላስተር አሰራር በማደጉ ለአገር ውስጥ የምግብ ዘይት ፋብሪካዎች አስተማማኝ የጥሬ እቃ ግብአት ዋስትና ፈጥሯል። በእንስሳት ሀብት ልማት በኩል የተጀመረው የሌማት ትሩፋት ብሔራዊ ኢኒሼቲቭ በአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ኑሮ ላይ ለውጥ ያመጣ ሌላኛው የስኬት ማሳያ ነው። በአፍሪካ ቀዳሚ የሆነውን የእንስሳት ሀብት ወደ ተጨባጭ ጥቅም ለመቀየር በተደረገው ጥረት የተሻለ ዝርያ ያላቸው የውጭና የሀገር ውስጥ ድቅል የወተት ላሞች ስርጭት በመጨመሩ፣ የዘመናዊ መኖ አቅርቦት በመሻሻሉ፣ እንዲሁም በከተማ ግብርና ጭምር በተስፋፋው የዶሮና የንብ እርባታ የወተት፣ የሥጋ፣ የእንቁላልና የንፁህ ማር ምርት በከፍተኛ ሁኔታ አድጓል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በታላላቅ ግድቦችና በሰው ሰራሽ ኩሬዎች ላይ እየተከናወነ ያለው የአሳ ሀብት ልማት ሥራ የሕዝቡን የሥነ-ምግብ (Nutritional) እና የፕሮቲን ፍላጎት ለማሟላት ትልቅ አቅም እየሆነ ይገኛል። የሆርቲካልቸር (የአትክልትና ፍራፍሬ) እና የኢኮኖሚ ሰብሎች ልማትም የሀገሪቱን የኤክስፖርት አድማስ ያሰፋ ሌላኛው ስኬታማ ዘርፍ ነው። የተሻሻሉ የአቮካዶ (Hass Avocado) እና የሙዝ ዝርያዎች በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በስፋት በመልማታቸው፣ ምርቶቹ በቀጥታ ወደ አውሮፓና መካከለኛው ምስራቅ ገበያ መላክ የጀመሩ ሲሆን፣ የሀገሪቱ ቀዳሚ የውጭ ምንዛሬ አስገኝ የሆነው ቡናም የአመራረት ዘዴው በመሻሻሉና በቀጥታ ለአምራቹ በሚከፈልበት የገበያ ትስስር (Vertical Integration) ምክንያት በየዓመቱ ከፍተኛ የምርትና የገቢ ሪከርድ እያስመዘገበ ይገኛል። የግብርናው ዘላቂነትና ምርታማነት የተረጋገጠው ደግሞ ቴክኖሎጂንና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃን በአግባቡ ማቀናጀት በመቻሉ ነው። መንግሥት ለትራክተሮች፣ ኮምባይነሮች እና የውሃ ፓምፖች ያደረገው የቀረጥ ነፃ መብት ተለምዷዊውን የእርሻ ስራ ወደ መካከለኛና ከፍተኛ ሜካናይዜሽን አሰራር የቀየረው ሲሆን፣ በቴክኖሎጂው ዘርፍ ድሮኖች (Drones) ለፀረ-ተባይ ርጭትና ለምርት ክትትል ጭምር ጥቅም ላይ መዋል ጀምረዋል። ይህ የቴክኖሎጂ ዕድገት በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከተከናወነው የተፈጥሮ ሀብትና የአፈር ጥበቃ ሥራ ጋር በመቀናጀቱ፣ የከርሰ ምድር ውሃ እንዲያገግም፣ የአፈር መሸርሸር እንዲቀንስና ለመስኖ ግብርና ምቹ ሁኔታ እንዲፈጠር አድርጓል። የተመዘገቡት ስኬቶች በሙሉ ዘላቂ የገበያ ዋስትና እንዲኖራቸው ለማድረግ የምርት ብክነትን ከሚቀንሱና እሴት ከሚጨምሩ የተቀናጁ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ጋር ሰፊ የገበያ ትስስር ተፈጥሯል። አርሶ አደሩ የሚያመርታቸው የሰብልና የእንስሳት ምርቶች በቀጥታ በሀገር ውስጥ ወደተገነቡት የምግብና መጠጥ ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎች እንዲገቡ መደረጉ፣ ለአርሶ አደሩ አስተማማኝ ገበያ ከመፍጠሩም በላይ ሀገሪቱ ከግብርና ምርት ጥሬ ዕቃ ላኪነት ወደ እሴት የተጨመረበት (Value-added) ምርት ላኪነት እንድትሸጋገር ትልቅ መዋቅራዊ መሠረት ጥሏል። በአጠቃላይ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የኢትዮጵያ ግብርና ሁሉንም ክፍሎች ያካተተ ሁለንተናዊ የብዝሃ-ዘርፍ ዕድገት በማስመዝገብ ላይ ይገኛል። ይህም የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተከናወነ ላለው ስራ ምቹ መደላድልን ፈጥሯል።
በክልሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ድጋፍ ሊጠናከር ይገባል
Jun 25, 2026 222
ጋምቤላ፤ ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለተያዘው ግብ መሳካት፣ የባለድርሻ አካላት ድጋፍና ትብብር ሊጠናከር እንደሚገባ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሯን ጨምሮ የክልልና የፌደራል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ በአቦቦ ወረዳ በሩዝ ሰብል ላይ እየተካሄደ ያለውን የምርምር ሥራ ዛሬ ጎብኝተዋል። ርዕሰ መስተዳድሯ በወቅቱ እንዳሉት፤ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚቻለው የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ማስፋፋትና ተደራሽ ማድረግ ሲቻል ነው። ክልሉ ያለውን ሰፊ የመሬትና የውኃ ሀብት በምርምር መደገፍ ከተቻለ፣ ለአካባቢው ብቻ ሳይሆን ለሀገር የሚተርፍ የሰብል ምርት ማግኘት እንደሚቻልም ተናግረዋል። ጋምቤላ ለሁሉም የግብርና ልማት ዓይነቶች ምቹ ሥነ-ምህዳር ያላት መሆኑን የጠቀሱት ወይዘሮ ዓለሚቱ፤ በተለይም የሩዝ ሰብል አዋጭ ተብለው ከተለዩት የሰብል ዓይነቶች በቀዳሚነት የሚጠቀስ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የሩዝ ልማትን ማዘመንና ማስፋፋት ከተቻለ ለአገር ውስጥ ፍጆታ አልፎ ለውጭ ገበያ የሚተርፍ ምርት ማግኘት እንደሚቻልም አክለዋል። ልማቱን ለመደገፍ በባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት፣ በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲና በቻይናው ዩናን ዩኒቨርሲቲ ቅንጅት እየተካሄደ ያለው የምርምር ሥራ የሚበረታታ መሆኑን በመግለጽ፣ ለሥራው ስኬታማነት የክልሉ መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍና ትብብር እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሀብት ልማት፣ የሥራ ስምሪትና የቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ እንደ ሀገር የታለመውን የግብርና ልማት ስኬታማ ማድረግ የሚቻለው አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለአርሶ አደሩና ለባለሀብቱ ተደራሽ ማድረግ ሲቻል መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም በተለያዩ ተቋማት ትብብር በሩዝ ሰብል ላይ የተጀመረው የምርምር ሥራ ተስፋ ሰጪና ዘርፉን የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል። የባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ካሳሁን ተስፋዬ በበኩላቸው፤ የምርምር ሥራው እየተካሄደ ያለው ከቻይናው ዩናን ዩኒቨርሲቲ ጋር መሆኑን አስረድተዋል። የአዲሱ የሩዝ ዝርያ ልዩ ባህሪያት መካከል በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚደርስ መሆኑ እንዲሁም በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ መመረቱ እንደሆነ ገልጸዋል። በሩዝ ዝርያዎቹ ላይ እየተካሄደ ያለው የማላመድ የምርምር ሥራ በሚቀጥለው ዓመት ተጠናቆ ለተጠቃሚዎች ተደራሽ እንደሚሆንም ዋና ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን ከ117 ሺህ በላይ ወጣቶችን የስራ እድል ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል- መምሪያው
Jun 25, 2026 159
ደብረ ማርቆስ ፤ሰኔ 18/2018(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን ባለፉት 11 ወራት ከ117 ሺህ በላይ ወጣቶች የስራ እድል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የዞኑ ስራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ፀሐይ ቦጋለ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ለበርካታ ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር የተቻለው የአካባቢውን ጸጋ በጥናት በመለየትና አልምቶ ለመጠቀም በተደረገ ጥረት ነው። በአጠቃላይ በበጀት ዓመቱ ከ 131 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር የታቀደ ሲሆን ባለፉት 11 ወራት 117 ሺህ 427 የሚሆኑ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። የተፈጠረው የስራ እድል በማዕድን ልማት ፣ በኮንስትራክሽን ፣ በግብርና ፣ በአምራች ኢንዱስትሪዎችና ሌሎች መስኮች መሆኑን ነው የጠቆሙት ። በዚሁ ወቅት የስራ እድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ከ30 በመቶ በላይ የሚሆኑት በተለያዩ መስኮች ትምህርታቸውን ተከታትለው የተመረቁ መሆናቸውንም አንስተዋል። የስራ እድል ለተፈጠረላቸው ዜጎች 491 ሚሊየን ብር በላይ ብድር፣ ከ270 በላይ የመስሪያ ሼድና ኮንቴነሮች ድጋፍ መደረጉን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም በገጠርና በከተማ በግብርና ዘርፎች ስራ ለተፈጠረላቸው ዜጎች ከ15 ሺህ ሄክታር በላይ የእርሻ መሬት በመስጠት ወደ ስራ ማስገባት መቻሉን አብራርተዋል። በዞኑ የባሶሊበን ወረዳ የጁቤ ከተማ ነዋሪ ወጣት ቀለምወርቅ ገነት ፤ ከሶስት ጓደኞቹ በመደራጀት ወደ ግብርና ስራ ገብቶ ተጠቃሚ መሆን መጀመሩን ነው የሚናገረው ። የተፈጠረለት የስራ እድል ከቤተሰብ ጥገኝነት በማውጣት ገቢ ለማግኝት ከማስቻሉ ባሻገር ሀብት ለማፍራት እንዳስቻለው ነው ያመለከተው። የአዋበል ወረዳ የሉማሜ ከተማ ነዋሪ ወጣት ጌትነት ይመር በበኩሉ፤በዘንድሮው ዓመት ከአምስት ጓደኞቹ ጋር በመደራጀት በኮንስትራክሽን ዘርፍ የብሉኬት ምርት ላይ መሰማራቱን ነው የሚናገረው። በመንግስት በተመቻቸላቸው የመስሪያ ቦታን ጨምሮ የ500 ሺህ ብር ብድርና ሌሎች ድጋፎች በመነሳት ወደ ስራ ተሰማርተው ገቢ ማግኝት መጀመራቸውን ነው የሚናገረው።