ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉ ስምምነቶች የአየር መንገዱን ዓለም አቀፍ ተደራሽነትና ገቢ ለማስፋት ጉልህ ሚና ይጫወታሉ
May 20, 2026 8
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉ የአየር አገልግሎት ስምምነቶች የአየር መንገዱን ዓለም አቀፍ ተደራሽነትና ገቢ በላቀ ደረጃ ለማሳደግ ጉልህ ሚና እንዳላቸው የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ከተለያዩ ሀገራት ጋር በተደረጉ የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ የአስረጂዎች መድረክ አካሂዷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ባንግላዲሽ፣ አንጎላ፣ ኢስዋቲኒና ሴራሊዮን በሚያደርጋቸው በረራዎች የተፈረሙ የሁለትዮሽ የአየር አገልግሎት ስምምነት እንዲሁም በኢትዮጵያና ቬትናም መካከል የዲፕሎማቲክ ወይም ኦፊሻል አገልግሎት ፓስፖርት ለያዙ ሰዎች ቪዛን ለማስቀረት የተፈረመው ስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ በዝርዝር ውይይት ተደርጓል። የቋሚ ኮሚቴው አባላትና የምክር ቤቱ የህግ ማእከል በስምምነቶቹ ፋይዳ፣ የበረራ ደህንነት መጠበቅ፣ በኢሚግሬሽን ቁጥጥር፣ የአየር መንገዶች ገንዘብ የመታገድ ችግር፣ የአየር መንገዶች የመሬት ላይ አገልግሎቶች ጋር የተያያዙ አስተያየቶችና ጥያቄዎችን አንስተዋል። ከሀገራቱ ጋር የተደረገው ስምምነት ከኢትዮጵያ ህገ-መንግስት፣ ከሌሎች ህጎች እንዲሁም ሀገሪቱ ካፀደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎች ጋር እንዳይጋጭ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ዲማ ነጎ (ዶ/ር)፥ ረቂቅ አዋጆቹን የሀገራትን ሉዓላዊነት ባከበረ መልኩ የሀገሪቱን ደህንነት በማስጠበቅና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን በማጠናከር በተለያዩ አማራጮች ሀገሪቱን ተጠቃሚ ለማድረግ ማዳበር እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። ስምምነቶቹ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚሰጠውን አገልግሎት ተወዳዳሪነት ለማላቅና የሀገሪቱን ጥቅም በማስጠበቅ ረገድ ከተለያዩ ህጎችና ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ጋር የተጣጣመ መሆኑን ደግሞ የውይይቱ ተሳታፊዎች አስረድተዋል። በኢትዮጵያ አየር መንገድ ዓለም አቀፍ ግንኙነት ተጠባባቂ ዳይሬክተር ጳውሎስ ኃይሌ፤ ከሀገራቱ ጋር የተደረጉ ስምምነቶች የአቪዬሽን ደህንነት፣ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ብሔራዊ ጥቅምን መሰረት ያደረጉ ናቸው ብለዋል። ስምምነቶቹ ለቱሪዝም፣ ንግድና ኢንዱስትሪዎች እድገት ጠቀሜታቸው ከፍ ያለ መሆኑን አንስተዋል። የአየር መንገዶች ገንዘብ የመታገድ ችግር ከባለድርሻ አካላት ጋር በዲፕሎማቲክ መንገድ እየተፈታ መሆኑን ገልጸዋል። አየር መንገዶች በተለያዩ ሀገራት የሚጠቀሟቸው የመሬት ላይ አገልግሎቶች የአየር መንገዶች አገልግሎት ብቃት ማሳያ መሆኑንና ከዓለም አቀፍ ስታንዳርዶች ጋር በተጣጣመ መልኩ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን የኢኮኖሚና ሬጉሌሽን ዳይሬክተር ናርዶስ በድሉ፤ ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የአየር መንገዱን ተደራሽነትና የትራፊክ መብቶችን የሚያሳድጉ እንዲሁም ተደራራቢ ቀረጥና ወጪን ለመቀነስ የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዓለም አቀፍ ህግ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል ይበቃል ግዛው፤ ከቬትናም ጋር የዲፕሎማቲክ ወይም ኦፊሻል አገልግሎት ፓስፖርት ለያዙ ሰዎች ቪዛን ለማስቀረት የተፈረመው ስምምነት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና የመወሰን ነጻነት የጠበቀ ነው ብለዋል።
በዞኑ የመሰረተ ልማት ተቋማት ግንባታን ከማስፋፋት ጎን ለጎን አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን ትኩረት ተደርጓል
May 20, 2026 66
መቱ ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በኢሉባቦር ዞን የመሰረተ ልማት ተቋማት ግንባታን ከማስፋፋት ጎን ለጎን የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ማሻሻል ትኩረት መደረጉን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በኢሉባቦር ዞን በበጀት ዓመቱ የተገነቡ 831 የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶችን ለአገልግሎት ክፍት የማድረግ መርሃ ግብር በሀሉ ወረዳ ተጀምሯል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ አስተዳደሩ ለሕብረተሰቡ ተጠቃሚነት የሚሰራ መሆኑን በተጨባጭ ስራዎች እያሳየ ነው። በዞኑ በትልቅ በጀት የሚሰሩ ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶችን በብዛትና በጥራት ለአገልግሎት በማብቃት ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም ተናግረዋል። በዚህም ዓመት በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የሕብረተሰቡን ጥያቄዎች የሚመልሱ፤ የአገልግሎት አሰጣጥ ቅሬታዎችን የሚፈቱ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተገንብተው ለአገልግሎት ክፍት መደረግ መጀመራቸውን ገልጸዋል። ከመሰረተ ልማት ተቋማት ግንባታ ጎን ለጎን የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ማሻሻል የተጀመሩ ስራዎች የሚጠናከሩ መሆኑን አስረድተዋል። ለምረቃ የበቁት ፕሮጀክቶችም የአስተዳደር ሕንጻዎች፣ ድልድዮች፣ የጤና ተቋማት፣ መንገዶች፣ የሶላር ኃይል ማመንጫ፣ የመጠጥ ውሃና የመስኖ ግድብ ፕሮጀክቶች መሆናቸውን ገልጸዋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነመራ ቡሊ፣ በክልሉ በበጀት ዓመቱ የበርካታ ፕሮጀክቶች ግንባታ መካሄዱን አስታውሰዋል። ፕሮጀክቶቹ የልማትና የአገልግሎት ተደራሽነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የሀሉ ወረዳ ነዋሪዎች ለአገልግሎት እየበቁ የሚገኙ ፕሮጀክቶች በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ያለውን አቅም የሚያሳድጉ፤ የሕብረተሰቡንም ማሕበራዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። የአስተዳደር ሕንጻው ብዙ ሴክተር መስሪያ ቤቶችን በአንድ ሕንጻ ውስጥ የሚሰበስብ እንደመሆኑ አገልግሎት ለማግኘት የሚጠይቀውን ድካም የሚቀንስ መሆኑን ተናግረዋል።
ክልሉን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ የህዝቡን አቅም አቀናጅቶ መጠቀም ይገባል
May 20, 2026 133
ጋቼኖ ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልልን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ የህዝቡን አቅም አቀናጅቶ መጠቀም እንደሚገባ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ በወላይታ ዞን ዳሞት ጋሌ፣ ዳሞት ፑላሳ ወረዳዎች እና ሻንቶ ከተማ የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በምረቃው ላይ እንደገለጹት፤ ክልሉን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ የህዝቡን አቅም አቀናጅቶ መጠቀም ይገባል። የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ የተጀመረው ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል። ዛሬ በወላይታ ዞን በዳሞት ጋሌና በዳሞት ፑላሳ ወረዳዎች እንዲሁም በሻንቶ ከተማ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች የዚሁ አካል መሆናቸውን አንስተዋል። በበጀት ዓመቱ ባለፉት 9 ወራት 275 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ትራንስፖርት እና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ተወልደ ተስፋዬ ናቸው። ዛሬ የተመረቀው የ15 ኪሎ ሜትር መንገድ በሻንቶ ከተማ፣ በዳሞት ፑላሳና በዳሞት ጋሌ ወረዳዎች የሚገኙ ቀበሌያትን የሚያገናኝ ነው ብለዋል፡፡ የሀርቶ ቆንጦላ ጫራቄ ተንጠልጣይ ድልድይ ደግሞ የዳሞት ጋሌና የዱጉና ፋንጎ ወረዳዎች ከ22 ሺህ በላይ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግም አስረድተዋል። የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ በበኩላቸው፤ በዞኑ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ለአገልግሎት ክፍት በመደረጋቸው የህዝቡ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። ለአብነትም የማህበረሰብ መድኃኒት ቤት ግንባታ ህዝቡ በቅርበትና በተመጣጣኝ ዋጋ መድኃኒት እንዲያገኝ ማገዙን ጠቁመዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ በመንገድና ድልድይ ማጣት ሁለቱ ወረዳዎች ተለያይተው እንደቆዩ ተናግረዋል። አሁን መንግስት ችግሩ እንዲፈታ በማድረጉ የጤና አገልግሎት ለማግኘትም ሆነ በቀላሉ ወደ ገበያ ሄዶ ለመገበያየት እንደቻሉም ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ቀደም መድኃኒት ለመግዛት ወደ ተለያዩ አካባቢዎች ርቀው ይጓዙ እንደነበርም ተናግረዋል። መድኃኒት ቤት በአቅራቢያቸው በመገንባቱ መድኃኒት በተመጣጣኝ ዋጋ እና በቅርበት ማግኘት በመቻላቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ የመንግስት ስራ ኃላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በክልሉ ለህብረተሰቡ የዘመናት ጥያቄ ምላሽ የሚሰጡ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት እየበቁ ነው-ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ
May 20, 2026 98
ሰመራ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦በአፋር ክልል ለህብረተሰቡ የዘመናት ጥያቄ ምላሽ የሚሰጡ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት እየበቁ መሆናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ ተናገሩ። ገቢ ረሱና ኸሪ ረሱ ዞኖችን እንዲሁም ወረዳዎችን ለማገናኘት የሚያስችሉ የጠጠር መንገዶችና ድልድይ በዛሬው ዕለት ተመርቋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እንዳሉት፤ መንግስት ለህብረተሰቡ ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ምላሽ እየሰጠ ይገኛል። ''ዛሬ ያስመርቅናቸው መንገዶችና ድልድይ ለረጅም ዘመናት በመንገድ ዕጦት ምክንያት ለተለያዩ ወጪዎች ተዳርጎ የቆየውን ህብረተሰብ በቅርብ ለማገናኘት የተቻለበት ነው'' ብለዋል። ይህ መንገድ ህብረተሰቡ ሲያነሳው የነበረውን ጥያቄ መመለስ የተቻለበት እና የህብረተሰቡ ተጠቃሚነት የተረጋገጠበት መሆኑን ገልፀው መሰል ስራዎችም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ ይህ እንዲሳካ ያደረገውን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር እንዲሁም የአካባቢውን ማህበረሰብ ለመንገዱ መጠናቀቅ ላደረገው ተሳትፎ አመስግነዋል። የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ መንግስት ለህብረተሰቡ ተጠቃሚነት በትኩረት እየሰራ ይገኛል። ''የአርብቶ አደር አካባቢዎችን የልማት ማዕከል ለማድረግ የመንገድ ልማት አስፈላጊ መሆኑን ተረድተን ውጤታማ ስራዎች እያከናወንን እንገኛለን" ብለዋል። አርብቶ አደሩ ማህበረሰብ ከዚህ በበለጠ ተጠቃሚነቱ እንዲጨምር በትብብር የሚሰሩ ተግባራት የሚጠናከሩ መሆኑንም አክለዋል። በዛሬው ዕለት ለተመረቁት የጠጠር መንገዶችና ድልድይ ስራ 433 ሚሊዮን ብር በመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስቴር የቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አማካኝነት ወጪ የተደረገባቸው መሆኑ ተመላክቷል።
የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ እየተከናወነ ያለው ተግባር ይጠናከራል-እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
May 20, 2026 97
ግንቦት ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ ከለውጡ ወዲህ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ እየተከናወነ ያለው ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) አስታወቁ። የክልሉ እና የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች በጉራጌ ዞን ከምሁር አክሊል ወረዳ ነዋሪዎች ጋር ህዝባዊ ውይይት አካሄደዋል። በወቅቱም የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)፤ የክልሉ መንግስት ለህዝቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ እየሰጠ መሆኑን አንስተዋል። ለተነሱ የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ማህበረሰቡን ባሳተፈ አግባብ ምላሽ እንደሚሰጥም ርዕሰ መስተዳድሩ አመልክተዋል። የወረዳውን የመስህብ ስፍራዎች እና ቅርሶች በአግባቡ በማልማትና በማስተዋወቅ የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንዲሁም የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ለማስፋፋት ከባለሃብቶች ጋር በመቀናጀት እንደሚሰራም ገልጸዋል። የምሁር ኢየሱስ ገዳም እና በዙሪያው ያሉ ቅርሶችን ለማልማት የተጀመሩ ስራዎችን ማጠናከር ከሁሉም እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። ባለሀብቶች በገዳሙ ዙሪያ የእንግዶች ማረፊያ በመገንባት ለዘርፉ እድገት አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱም ጥሪ አቅርበዋል። የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳደሪ አቶ ላጫ ጋሩማ በበኩላቸው በአካባቢው፤ ያለውን ፀጋና ሀብት በመጠቀም የህብረተሰቡን ኑሮ በማሻሻል ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ እየተከናወነ ያለው ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ ሰፋፊ ኢንቨስትመንቶችን በመሳብ ለወጣቶች የስራ እድል ፈጠራን የሚያሰፉ ኢንዱስትሪዎች ትኩረት እንደተሰጣቸው አመልክተዋል። የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ ብስራት ገብሩ በበኩላቸው ከለውጡ ወዲህ የአካባቢን ጸጋ በማልማት የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። በወረዳው የህዝብ ጥያቄዎችን ለመፍታት በንፁህ መጠጥ ውሃ፣ በጤና ዘርፍ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በውይይት መደረኩ ላይ የተሳተፉ ከፍተኛ የክልሉና የዞኑ አመራሮች በዞኑ ምሁር አክሊል ወረዳ የሚገኘውን ታሪካዊው የምሁር እየሱስ ገዳምን ጎብኝተዋል።
በክልሉ በለውጡ ዓመታት የህዝብን የልማት ጥያቄ መሰረት ያደረጉ የተለያዩ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል
May 20, 2026 88
ወንሾ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል በለውጡ ዓመታት የህዝብን የልማት ጥያቄ መሰረት ያደረጉ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ስራዎች መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ በማዕከላዊ ሲዳማ ዞን ወንሾ ወረዳ የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶችን ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። በምረቃው ላይ ርዕሰ መስተዳድሩ እንደገለጹት፣ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በክልሉ የህዝብን የልማት ጥያቄ መሰረት ያደረጉ ዘርፈ ብዙ የመሰረተ ልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። በዚህም ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተጨባጭ ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቅሰው፣ በልማት ሥራዎቹ የህብረተሰቡ የተቀናጀ ተሳትፎ ጉልህ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ የተመረቁ የልማት ፕሮጀክቶች የክልሉ መንግስትና በየደረጃው ያሉ መዋቅሮች በቅንጅት ያስመዘገቡት ውጤት ነው ብለዋል። የልማት ፕሮጀክቶቹ የአገልግሎት አሰጣጥን በማሳለጥ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች የሚፈቱ መሆናቸውንም አስታውቀዋል። የወንሾ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ወልዴ ዩምራ በበኩላቸው፤ በወረዳው የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸውና ህዝቡም የተሳተፉባቸው ናቸው ብለዋል። ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ከበቁ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶቹ መካከል ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት፣ የወረዳ አስተዳደር ሕንጻ እና ሌሎች አገልግሎት የሚያሳልጡ የመንግስት ተቋማት እንደሚገኙበትም አመልክተዋል። የአካባቢው ህብረተሰብ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎችን በሂደት የመመለስ አቅም እያደገ መምጣቱን ገልጸው፣ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የአካባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ ሽታዬ እሳቱ፤ የለውጡ መንግስት ህብረተሰቡን በማስተባበር ባከናወናቸው የልማት ፕሮጀክቶች ህዝቡ ተጠቃሚነቱ እየተረጋገጠ መጥቷል። ዛሬ የተመረቁ ፕሮጀክቶችም አገልግሎትን የሚያሳልጡና የወረዳውን እድገት የሚያፋጥኑ ናቸው ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደ፣ የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አብርሃም ማርሻሎ እንዲሁም ሌሎች የክልሉና የፌደራል መንግስት የሥራ ሃላፊዎችና የህብረተሰብ ክፍል ተወካዮች ተገኝተዋል።
ከተረጂነት ወጥተን በጀመርነው የገቢ ማስገኛ ሥራ ተጠቃሚ ሆነናል-አርሶ አደሮች
May 20, 2026 79
ሀዋሳ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ከምግብ ዋስትና ፕሮግራም ተረጂነት ወጥተው በጀመሩት የገቢ ማስገኛ ሥራ ተጠቃሚ ከመሆን ባለፈ ለሌሎችም እንደተረፉ አርሶ አደሮች ገለጹ። ግብርና ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋር በመተባበር "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በሃዋሳ ባዘጋጀው መድረክ ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ አርሶ አደሮች እንዳሉት፤ በገቢ ማስገኛ ሥራ ላይ መሰማራታቸው ተጠቃሚ አድርጓቸዋል። ከዚህ ቀደም በምግብ ዋስትና መርሀግብር ታቅፈው በሚያገኙት አነስተኛ ገቢ ህይወታቸውን ይመሩ እንደነበር አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የሥራ ዘርፎች በመሰማራት ውጤታማ ከመሆን ባለፈ ለሌሎች መትረፍ እንደቻሉ ተናግረዋል። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስልጤ ዞን ስልጢ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ሙዲ ሀሰን እንዳሉት፤ ለዓመታት በፕሮግራሙ ታቅፈው በሚያገኙት አነስተኛ ገቢ ሕይወታቸውን ሲመሩ ቆይተዋል። በአካባቢያችን 65 ነዋሪዎች በመርሀግብሩ ድጋፍ ሲደረግልን ቆይተናል ያሉት አርሶ አደሩ፣ ከእነዚህ ውስጥ15ቱ በማህበር ተደራጅተው በንብ ማነብ እና በቅመማ ቅመም ልማት ሥራ መሰማራታቸውን ገልጸዋል። የንብ ማነብ ሥራውን በ25 ዘመናዊና ባህላዊ ቀፎ ታግዘው እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸው፣ በአንድ ተኩል ሄክታር ማሳ ላይም ሮዝመሪ በማልማት 300 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። በስልጤ ዞን ሁልባረግ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ካይሻ ኤርጌቾ፤ አካል ጉዳተኛ በመሆናቸው ለዓመታት በፕሮግራሙ በተደረገላቸው ድጋፍ ህይወታቸውን ሲመሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። በምግብ ዋስትና ፕሮግራም ያገኙትን ገንዘብ በመቆጠብ በጀመሩት የሱቅ እና አነስተኛ ግብርና ሥራ ገቢያቸውን በማሳደግ ከእርዳታ ሙሉ በሙሉ መውጣታቸውን ተናግረዋል። በሀላባ ዞን የሲምቢጣ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ገረመው መሀመድ፤ በቀበሌያቸው በተከሰተ የጎርፍ አደጋ ምክንያት ለዓመታት ከቀዬያቸው በመፈናቀል ለተረጂነት ተዳርገው እንደነበር አስታውሰዋል። በተደረገላቸው ድጋፍ ታግዘው በተለያዩ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሥራ መሰማራታቸውን ገልጸው፣ በዚህም ከተረጂነት ወጥተው በተለያየ አካባቢ መኖሪያ ቤቶችን በመገንባት ሀብት ማፍራታቸውን ጠቅሰዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጌዴኦ ዞን ኮቾሬ ወረዳ ነዋሪው ወጣት አርሶ አደር ታሪኩ ታደሰ በበኩሉ እንዳለው፣ ቀደም ሲል ምንም አይነት ገቢ ስላልነበረው በምግብ ዋስትና ፕሮግራም ሰርቶ በሚያገኘው አነስተኛ ገቢ ይተዳደር ነበር። በአሁኑ ወቅት በቡና እና በሥራ ሥር ተክሎች ልማት ተሰማርቶ ገቢውን በማሳደግ 2 ሚሊዮን ብር ሀብት ማፍራቱን ተናግሯል። በእዚህም ከእርዳታ ተላቆ ከራሱ ባለፈ በአቅራቢያው አቅመ ደካማ ቤተሰብ እያገዘ መሆኑንም ገልጿል። ከሲዳማ ዞን ሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ቱላ ቀበሌ የነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ዴቢቴ ናሮ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በመርሀግብሩ ያገኙትን ገንዘብ በመቆጠብ በጀመሩት የዶሮና ፍየል እርባታ ሥራ ከእርዳታ ተላቅቀዋል። በአሁኑ ወቅትም ያረቧቸውን ፍየሎች ለሌሎች በመስጠት ተጠቃሚ እንዲሆኑ እያገዙ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በኦሮሚያ ክልል በመኸር አዝመራ እስካሁን 6 ነጥብ 7 ሚሊየን ሄክታር የመሬት ዝግጅት ተደርጓል
May 20, 2026 162
ጅማ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በመኸር አዝመራ ለማልማት ከታቀደው መሬት እስካሁን 6 ነጥብ 7 ሚሊየን ሄክታር የመሬት ዝግጅት መደረጉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በዛሬው ዕለት የክልሉ ግብርና ቢሮ አመራሮች እና የጅማ ዞን የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በዞኑ ቦተር ጦላይ ወረዳ ለመኸር አዝመራ እርሻ የተዘጋጀ መሬትን በበቆሎ ዘር የመሸፈን ሥራ ተጀምሯል። የቢሮው ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ በወቅቱ እንዳሉት፤ በክልሉ በዘንድሮው የመኸር አዝመራ 11 ነጥብ 1 ሚሊየን ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። በእስካሁኑ ሂደትም በመኸር አዝመራ ለማልማት ከታቀደው አጠቃላይ መሬት 6 ነጥብ 7 ሚሊየን ሄክታር የሚሆነው መሬት ተዘጋጅቷል ብለዋል። ዘንድሮ የግብርና ግብዓቶች ለአርሶ አደሩ ቀደም ብለው እየቀረቡ በመሆናቸው በመኸር የተሻለ ውጤት እንደሚገኝ ተስፋ ተጥሏል ነው ያሉት። በክልሉ ግብርናን በሜካናይዜሽን ለማስፋፋት ባለፉት ዓመታት በቴክኖሎጂ የታገዘ ሥራ ሲሠራ መቆየቱን አስታውሰው፣ በዚህ ዓመት ብቻ 1 ሺህ 200 ትራክተሮች ለክልሉ አርሶ አደሮች መድረሳቸውን ገልጸዋል። በዚህ ወቅትም አጠቃላይ በክልሉ ከ11 ሺህ በላይ ትራክተሮች የግብርና ሥራውን በማቀላጠፍ ላይ ይገኛሉ ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪም ለዘንድሮ እርሻ ለአርሶ አደሩ ለማቅረብ ከታቀደው 10 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ 7 ሚሊየኑ ወደ ክልሉ የገባ ሲሆን፣ 3 ሚሊየን የሚሆነው ተሰራጭቷል ብለዋል። የጅማ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ዩሱፍ ሻሮ በዞኑ ለአርሶ አደሮች ቀደም ብሎ የግብርና ግብዓቶች እንዲቀርቡ መደረጉን ተናግረው፣ በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ 883 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዷል ብለዋል። አጠቃላይ ከሚለማው መሬት ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ዘር የሚለማ መሆኑንም ጠቅሰዋል። የቦቶር ጦላይ ወረዳ አርሶ አደር ከበደ ታየ በ7 ሄክታር መሬት ላይ በቆሎ የማልማት ሥራ መጀመራቸውን ገልጸው፣ በኩታ ገጠም ማረሳቸው ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል። አርሶ አደሩ ዘንድሮ በቂ የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ በማግኘታቸው ብዙ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል። ሌላኛው አርሶ አደር ኡመር ቃሲም ከዚህ ቀደም በኩታገጠም በማልማት ከአንድ ሄክታር 75 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን ተናግረው በትራክተር ታግዘው በማረስ መሬታቸውን በዘር የመሸፈን ስራ መጀመራቸውን ገልፀዋል። በዘንድሮ እርሻ ለአርሶ አደሮች አስፈላጊ ሙያዊ እገዛ እየተደረገ መሆኑም ተመላክቷል።
ከተሞችን በማዘመን የእድገት ምንጭ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
May 20, 2026 89
ደብረ ብርሃን፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የሚገኙ ከተሞችን በማዘመን ለእድገት መሰረት እንዲሆኑ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሐመድ (ዶ/ር ) ገለጹ፡፡ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በደብረ ብርሃን ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሐመድ (ዶ/ር ) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ መንግስት ከተሞችን በማዘመን ለኢንቨስትመንት ፣ ለቱሪዝምና ለኑሮ ምቹ እንዲሆኑ ያከናወናቸው ተግባራት ውጤት እየተመዘገበባቸው ነው። በከተሞች ተገንብተው የተጠናቀቁና በመገንባት ላይ ያሉ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ለምጣኔ ሃብት እድገት መሰረት እየጣሉ መሆኑንም አረጋግጠዋል። በደብረ ብርሃን ከተማ በመገንባት ላይ የሚገኙ የኮሪደር ልማት፣ የአስፋልት መንገድ፣ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ግንባታና ሌሎች የመሰረተ ልማት ስራዎች ለዚህ ማሳያ ናቸው ብለዋል። የደብረ ብርሃን ከተማን ለኢንዱስትሪ፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ተመራጭ እንድትሆን ለማድረግም የመሰረተ ልማት ግንባታ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት በበኩላቸው፤ ከተማዋ ለአምራች ኢንዱስትሪ ያላትን ተመራጭነት በመጠቀም የማምረት አቅምን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በዛሬው እለት የተጎበኙትም የሶስት ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት፣ ከሁለት ነጥብ ሰባት ኪሎ ሜትር በላይ የአስፋልት መንገድን ጨምሮ የሶስት ኪሎ ሜትር የድንጋይ ንጣፍ መንገዶች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም 56 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱን ጠቁመው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ግንባታን በማጠናቀቅ የኔትወርክ ዝርጋታ እየተከናወነ እንደሚገኝም አስረድተዋል። የልማት ፕሮጀክቶቹም በከተማ አስተዳደሩና በነዋሪዎች የጋራ ትብብር እየተገነቡ የሚገኙ መሆናቸውን አስገንዝበዋል።
ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ ለማቅረብ የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል
May 20, 2026 92
ቃሉ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ ለማቅረብ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለፁ። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በደቡብ ወሎ ዞን ቃሉ ወረዳ በ365 ሚሊዮን ብር የተገነባውን ዲርማ ወንዝ መስኖ ፕሮጀክት ዛሬ መርቀዋል። በፕሮጀክቱ ምረቃ ላይ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በክልሉ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው። በተለይም ግብርናውን በሜካናይዜሽን፣ በቴክኖሎጂና በአዳዲስ አሰራር በማዘመን የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ የሚቀርብ ምርት ለማምረት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የገፀ ምድርና የከርሰ ምድር ውሃ በስፋት እንደሚገኝ ጠቅሰው፣ ይሄን የውሃ ሀብት ለመስኖ ልማት በማዋል ዓመቱን ሙሉ የማምረት ሥራው ይጠናከራል ብለዋል። ለእዚህም በክልሉ በርካታ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ ሥራ እየተከናወነ ነው ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በቃሉ ወረዳ ዛሬ የተመረቀው ፕሮጀክትም ለእዚህ አንዱ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል። ፕሮጀክቱ በደቡብ ወሎ ዞን የቃሉ ወረዳ እና በኦሮሞ ብሔረሰብ ዞን የደዋጨፋ ወረዳን በጋራ የልማት ተጠቃሚ የሚያደርግ በመሆኑ ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ፋይዳው የጎላ ነው ሲሉም አክለዋል። የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የመስኖ መሰረት ልማቶችን በማስፋፋት አርሶ አደሩ ከዝናብ ጠባቂነት ተላቆ በመስኖ ጭምር በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ በማምረቱ ውጤት እያስገኘ ነው። በቃሉ ወረዳ በ365 ሚሊዮን ብር ተገንብቶ ዛሬ የተመረቀው የመስኖ ፕሮጀክት ከ290 ሄክታር በላይ መሬት በመስኖ ለማልማት የሚያስችልና ከ490 በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን አስታውቀዋል። ግንባታው በሰባት ወራት ጊዜ ውስጥ መጠናቀቁ የመንግስትን ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ጀምሮ የመፈጸም ብቃት ያሳያል ብለዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮንን፤ በዞኑ የሚገነቡ በርካታ የመስኖ ፕሮጀክቶች ምርታማነትን በማሳደግ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ዛሬ የተመረቀው የመስኖ ፕሮጀክት አርሶ አደሩ በዓመት ሦስት ጊዜ በማምረት ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ የሚያስችለው መሆኑን የገለጹት ደግሞ የቃሉ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሙህዲን አህመድ ናቸው። በምረቃው ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
የከርሰ ምድር ውኃን በመጠቀም በበጋ ስንዴ መስኖ ውጤታማ ለመሆን እየሰራን ነው
May 20, 2026 243
ሮቤ፣ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፡- በባሌ ዞን የከርሰ ምድር ውኃን በራሳቸው አቅም በማውጣት በበጋ ስንዴ መስኖ ልማት ውጤታማ ለመሆን እየሰሩ መሆናቸውን የአጋርፋ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ። የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ በበኩሉ በአርሶ አደሩ እየተከናወኑ የሚገኙ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ኢኒሼቲቮችን ይበልጥ ውጤታማ የሚያደርግና የሚያዘምን የምርምር ፕሮጀክት እየተገበረ መሆኑ ተመልክቷል። በዞኑ የአጋርፋ ወረዳ አርሶ አደሮች እንደሚሉት ዩኒቨርሲቲው በምርጥ ዘር አቅርቦት ድጋፍና በፍትሃዊ የውኃ አጠቃቀም ላይ ሙያዊ ድጋፍ እያደረገላቸው መሆኑን አመልክተዋል። በልማቱ እየተሳተፉ ካሉ የወረዳው አርሶ አደሮች መካከል አቶ ሐሰን አህመድ በሰጡት አስተያየት፣ ከዚህ በፊት የዝናብ ውኃን ብቻ በመጠበቅ ስንዴና ሌሎች የግብርና ልማቶችን ያካሂዱ እንደነበር ተናግረዋል። ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ ከዝናብ ውኃ በተጨማሪ በአካባቢያቸው የሚገኘውን የከርሰ ምድር ውኃን በራሳቸው አቅም በማውጣትና በመጠቀም ስንዴን በማልማት ይበልጥ ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን አመልክተዋል። አርሶ አደር ሐሰን እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው በፍትሃዊና ዘመናዊ የመስኖ ውኃ አጠቃቀም ላይ በተግባር የተደገፈ እገዛ እያደረገላቸው በመሆኑ ከአንድ ሄክታር እስከ 55 ኩንታል ስንዴ እንደሚጠብቁ አመልክተዋል። ዩኒቨርሲቲው በምርጥ ዘር አቅርቦትና በመስኖ ዘርፍ የሚያጋጥሙንን ችግሮች እንዲፈቱልን እየደገፈን ስለሆነ የተሻለ ምርት ለማግኘት ተግተን እየሰራን ነው ያሉት ደግሞ ሌላው የወረዳው አርሶ አደር ሁሴን መሐመድ ናቸው። አቶ ሁሴን እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው በባለሙያ ምክርና እገዛ የተለያዩ የውሃ አማራጮችን በቁጠባ እንዲጠቀሙ እንዳገዛቸው ገልጸው፤ በማሳቸው ላይ የተለያዩ የስንዴ ዝርያዎችንም በማላመድ ለአካባቢው ተስማሚ የሆኑትን እንዲመርጡ ድጋፍ እያደረገላቸው መሆኑን ነው የገለጹት። በዩኒቨርሲቲው የስንዴ ምርምር ፕሮጀክት ዋና አስተባባሪና ተመራማሪ ጀማል አብዱልከሪም (ረዳት ፕሮፌሰር) በበኩላቸው እንደገለጹት፣ ዩኒቨርሲቲው በአርሶ አደሩ እየተከናወኑ የሚገኙ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ኢኒሼቲቮችን ይበልጥ ውጤታማ የሚያደርግና የሚያዘምን የምርምር ፕሮጀክት እየተገበረ ነው። ምርምሩ በዋናነት ቴክኖሎጂን በመጠቀም ለበጋ ስንዴ ልማት የሚያስፈልገውን የውኃ መጠንና የጊዜ ሰሌዳ ይወስናል ብለዋል። “ይህንን ቴክኖሎጂ በመጠቀም የተለያዩ የስንዴ ዝርያዎችን በቦይ መስኖ እና በርጭት መስኖ ዘዴዎች መካከል የሚታዩ ልዩነቶችን አርሶ አደሩ እንዲረዳ በማሳው ላይ በተግባር እየፈተሽን እንገኛለን” ብለዋል። አርሶ አደሩ በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገሩና ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችን ራሱ መርጦ እንዲያመርት ለማድረግ ያለሙ የተለያዩ ዝርያዎች ብዜቶች እየተካሄዱ መሆኑንም አክለዋል። የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ብርሃነመስቀል ጠና (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ዩኒቨርሲቲው የአካባቢውን ማህበረሰብ ችግርና ፍላጎት መሰረት ያደረጉ የምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። የዩኒቨርሲቲው ተመራማሪዎች በስንዴ ምርምር ላይ በባሌና ምዕራብ አርሲ ዞኖች እያደረጓቸው የሚገኙት የቴክኖሎጂ ሽግግር ተግባራትም የዚሁ ማህበረሰብን የመለወጥ ትልቅ ጥረት አካል መሆናቸውን ፕሬዚዳንቱ አረጋግጠዋል። ይህ የምርምር ፕሮጀክት በመስኖ ውኃ አጠቃቀም መስክ የሚስተዋሉ ችግሮችን በመፍታት፣ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በዘርፉ የተሰማሩ አርሶና አርብቶ አደሮች ተጠቃሚነትን ይበልጥ ለማጉላት ዓላማ ማድረጉን አመልክተዋል። የምርምር ፕሮጀክቱ የአሜሪካው ‘Grow Further’ ከተባለ ድርጅት ጋር በመቀናጀት በመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ እየተሰራ ያለ ሲሆን፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን የበጋ መስኖ ስንዴ ምርት ማነቆዎችን ለመፍታት ያለመ መሆኑ ገልጸዋል። በባሌ ዞን በአሁኑ ወቅት ከ150 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት በበጋ መስኖ እየለማ መሆኑ ተገልጿል።
የከሰም መስኖ ግድብ ማሻሻያ ግንባታ መጠናቀቅ የጎርፍ አደጋ ስጋትን በዘላቂነት ይቀርፋል-ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)
May 20, 2026 140
ሰመራ፣ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦የከሰም መስኖ ግድብ የማሻሻያ ግንባታ መጠናቀቅ ከሚሰጠው ዘላቂ የልማት አገልግሎት ባሻገር፣የአካባቢውን ማህበረሰብ ለዓመታት ሲፈታተን የነበረውን የጎርፍ ስጋት ሊቀርፍ የቻለ ወሳኝ ፕሮጀክት መሆኑን የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) አስታወቁ። የከሰም መስኖ ግድብ የጥገና ማሻሻያ ፕሮጀክት የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እና የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብረሃም በላይ (ዶ/ር) በተገኙበት ትናንት በይፋ ተመርቆ ስራ ጀምሯል። በዚህ ወቅት ሚኒስትር አብረሃም(ዶ/ር) እንዳሉት፥ የከሰም መስኖ ግድብ ቀደም ሲል በአካባቢው ማህበረሰብ ዘንድ እንደ ትልቅ ስጋት ይታይ ነበር። ግድቡ ከዚህ ቀደም ይፈጥር ከነበረው የአደጋ ስጋት ተላቆ ለአካባቢው ነዋሪዎች አስተማማኝና ጠቃሚ የልማት መሠረተ-ልማት መሆን የቻለው በተደረገለት ስልታዊ የኢንጂነሪንግ ጥገናና ማሻሻያ አማካኝነት መሆኑን ገልጸዋል። በአካባቢው ማህበረሰብ የነበረውን የአደጋ ስጋት በመቅረፍ ግድቡን ለታለመለት የመስኖ ልማት ለማዋል ለተከናወነው የጥገናና ማሻሻያ ፕሮጀክትም 2 ቢሊዮን ብር በጀት መውጣቱን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የከሰም መስኖ ግድብ የውሃ ፍሰት በተመጣጣኝና ቁጥጥር በተደረገበት ሁኔታ እንዲለቀቅ በማድረግ፣ ለአካባቢው የግብርና ሥራዎች ሙሉ በሙሉ አገልግሎት ላይ እንዲውል መደረጉን ገልጸዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እንዳሉት፥ ተጠግኖ ወደ አገልግሎት የገባው ግድቡ ህብረተሰቡን ከስጋት ያዳነ እና በርካታ ጥቅሞች ያሉት ነው። በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድ ይስተዋል የነበረውን ስጋት በማስወገድ ረገድ የተከናወነው ሥራ ውጤታማ መሆኑን የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ የግድቡ ጥገና መጠናቀቅ የማህበረሰቡን የቆየ ጥያቄ የፈታ መሆኑንም ተናግረዋል።
በክልሉ በልማታዊ ሴፍትኔትና ምግብ ዋስትና የታቀፉ ወገኖች ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ ነው
May 20, 2026 65
ባህር ዳር ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ከ231 ሺህ በላይ ወገኖች በከተማ ሴፍትኔትና ምግብ ዋስትና ፕሮግራም ታቅፈው ሃብት በማፍራት ላይ መሆናቸውን የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ገለፀ። የቢሮ ኃላፊው ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በከተሞች የምግብ ዋስትናን በዘላቂነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት በትብብር እየተከናወኑ ይገኛል። በዚህም ከ195 ሺህ በላይ አነስተኛ ገቢ ያላቸውን ወገኖች በከተሞች በሚከናወኑ የልማት ስራዎች በማሳተፍ የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥም ባለፈ በዘላቂነት ሃብት እንዲያፈሩ እየተደረገ ይገኛል። ተጠቃሚዎቹ በ18 ከተሞች በአረንጓዴ እና በተፋሰስ ልማት፣ በከተማ ፅዳትና ውበት፣ በማህበራዊ ተቋማት ግንባታና መሰል የልማት ስራዎች እንዲሳተፉ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ተጠቃሚዎቹ በተሰማሩበት መስክ በየወሩ ከሚያገኙት ክፍያ በተጨማሪም ከፕሮግራሙ ሲመረቁ በዘላቂነት በገቢ ማስገኛ ስራዎች እንዲሳተፉ እየተደረገ ነው ። በተለይም በሰብል ልማት፣ በቁም እንስሳት ማድለብ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በጨርቃጨርቅና አልባሳት፣ በቆዳ ውጤቶች ስራና መሰል ዘርፎች እንዲሳተፉ በማድረግ ሃብት እንዲያፈሩ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በተጨማሪም ከ36 ሺህ በላይ አቅመ ደካሞች፣ የጤና ችግር ያለባቸውና ደጋፊ የሌላቸው ወገኖች በቀጥታ ድጋፍ ተጠቃሚ እየተደረጉ መሆኑን ገልፀዋል። በተያዘው ዓመትም በፕሮግራሙ ታቅፈው ድጋፍ ሲደረግላቸው የቆዩና ተጨባጭ ለውጥ ያስመዘገቡ 18 ሺህ ተጠቃሚዎች ከፕሮግራሙ መመረቃቸውን አረጋግጠዋል። ፕሮግራሙ የበርካታ ወገኖችን ኑሮ ከማሻሻሉም በላይ በከተሞች የሚከናወነውን ልማት እንዲፋጠን የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሆነም አብራርተዋል። የፕሮግራሙ ውጤታማነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ጠቅሰው፤ ቀጣይም የበለጠ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። ለፕሮግራሙ ማስፈፀሚያ ከ3 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ተይዞለት እየተተገበረ ሲሆን 39 ሺህ ወገኖች ከፕሮግራሙ ማስመረቅ እንደተቻለ ሃላፊው ጨምረው አስታውቀዋል። በባህር ዳር ከተማ በፕሮግራሙ ታቅፈው ተጠቃሚ የሆኑት ወይዘሮ አስናቀች ደምለው እንዳሉት፤በፕሮግራሙ ተሳታፊ በመሆን በጀመሩት ቁጠባና የመቋቋሚያ ገንዘብ አሁን ላይ በሸቀጣሸቀጥ ንግድ ተሰማርተው እየሰሩ ይገኛል። ቀደም ሲል ኑሯቸው ከእጅ ወደ አፍ እንደነበረ አስታውሰው፤ አሁን ላይ በሚያገኙት ገቢ ቤተሰባቸውን በአግባቡ ከማስተዳደር ባለፈ ሃብት በማፍራት ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል። በፕሮግራሙ ለሦስት ዓመታት በልማት ስራ ሲሳተፉ የቆየቱ ወይዘሮ ኤልሳ አሻግሬ ባስመዘገቡት ውጤት ተመርቀው በራሳቸው የንግድ ስራ ላይ መሰማራታቸውን ይገልፃሉ፡፡ አሁኑ ወቅትም በተደረገላቸው ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ሃብት ለማፍራት መቻላቸውን ተናግረዋል።
አረንጓዴ አሻራ ሀገራዊ የንብ ሃብት መጠንን በማሳደግ የማር ምርትና ጥራት እንዲጨምር ጉልህ አስተዋጾ አድርጓል
May 20, 2026 74
ዲላ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፡-የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ሀገራዊ የንብ ሃብት መጠንን በማሳደግ የማር ምርትና ጥራት እንዲያድግ ጉልህ አስተዋጾ እያደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ የንብ ልማት ማህበር አስታወቀ። ዓለም አቀፍ የንብ ቀን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደረጃ በዲላ ከተማ ሲከበር ኢዜአ ያነጋገራቸው ባለድርሻ አካላት እንዳሉት ከተወሰኑ ዓመታት ወዲህ ለንብ ሃብት ልማት ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል። በየዓመቱ የሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብርም፣ ሀገራዊ የንብ ሃብት መጠንን በመጨመር የማር ምርትና ጥራት እንዲያድግ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ተገልጿል። መርሀግብሩ የተፈጥሮ ሚዛንን ከመጠበቅ ባለፈ የሥነ ምግብ ይዘትን ለማሻሻል ጉልህ አስተዋጾ እያበረከተ መሆኑም ተመላክቷል። የኢትዮጵያ የንብ ልማት ማህበር ዋና ሥራ አስኪያጅ ነጋሽ በቀና በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ መንግስት ለንብ ሃብት የሰጠው ትኩረት የዘርፉን እምቅ አቅም አውጥቶ ለመጠቀም እያስቻለ ነው። በተለይ የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብርን ጨምሮ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ሥራዎች የንብ ሃብት መጠንን በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ እያገዙ መሆኑን ተናግረዋል። የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራው ከሌማት ትሩፋት ትግበራ ጋር ተዳምሮ የተፈጥሮ ሚዛንን ከመጠበቅ ባለፈ የማር ምርት ጥራትና ይዘትን አሻሽሏል ብለዋል። የክልሉን እምቅ የንብ ሃብት ልማት በአግባቡ ለመጠቀም የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ሃላፊና የእንስሳትና አሣ ሃብት ልማት ዘርፍ ሃላፊ አባይነህ ከዳ (ዶ/ር) ናቸው። በተለይ የንብ መንጋ ብዜት ማዕከላትን በማስፋፋትና አርሶ አደሩን በመንደር በማደራጀት በተደረገ የግብዓትና የክህሎት ድጋፍ የዘርፉን ምርታማነት ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። በዚህም በተያዘው በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ከ17 ሺህ ቶን በላይ ጥራቱን የጠበቀ ማር ለገበያ መቅረቡን በማሳያነት ጠቅሰዋል። በጌዴኦ ዞን ወናጎ ወረዳ የአንድነት ንብ ልማት ማህበር ሰብሳቢ ወይዘሮ ብርቱካን ተስፋዬ በበኩላቸው 12 ሆነው በማህበር በመደራጀት በንብ ልማት ሥራ መሰማራታቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት ማህበሩ ባለው ከ50 በላይ ዘመናዊና ባህላዊ የንብ ቀፎ በዓመት ከ1 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ ማር በማምረት ለገበያ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የማህበሩ አባላት ከራሳቸው ባለፈ ቤተሰቦቻቸውን በመርዳት ለሌሎች ወጣቶች አርአያ የሚሆን ተግባር እያከናወኑ መሆኑንም አመልክተዋል።
በሀዋሳ ከተማ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች የኢንዱስትሪውን ምርታማነት አሳድጓል
May 20, 2026 81
ሀዋሳ፤ ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)--በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪውን ምርታማነት ማሳደግ እንደተቻለ የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ኢንዱስትሪ ልማት መምሪያ አስታወቀ። የመመሪያው ሃላፊ አቶ በሀይሉ ጌታቸው ለኢዜአ እንደገለጹት በከተማው የአምራች ኢንዱስትሪውን ምርታማነት ለማሳደግ ከሀይል አቅርቦት ጋር የሚነሱ ችግሮችንና መሰረተ ልማቶች ለማሟላት በተቀናጀ መንገድ ተሰርቷል፡፡ በዚህም በበጀት ዓመቱ እስካሁን ድረስ 70 አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ በመግባት ከ9 ሺህ 800 በላይ ለሚሆኑ ዜጎችም የሥራ ዕድል መፈጠራቸውን ተናግረዋል። ኢንዱስትሪዎች ምርቶቻቸውን የሚያስተዋውቁበትና የገበያ ትስስር የሚፈጥሩበትን ኤግዚብሽንና ባዛሮችን በማዘጋጀት ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉንም ነው አቶ በሀይሉ አመልክተዋል። የአብርሽና ቤተሰቡ የቆዳና ቆዳ ውጤቶች አምራች ኢንዱስትሪ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ከድር አህመድ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኢንዱስትሪው እየገጠሙት ያሉትን ችግሮች በተቀናጀ መልኩ ለመፍታት እያስቻለ መሆኑን ጠቁመዋል። በአስተዳደሩ በኩል የድጋፍና ክትትል ሥርዓት በመጠናከሩ የዓለም አቀፍ ገበያን ደረጃ የሚያሟሉ የቆዳ ምርቶች እያመረቱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የሀይል አቅርቦት ችግር እየተፈታ መምጣትና ለኢንዱስትሪዎች በተለያያ መንገድ የገበያ ትስስር መፈጠሩ ለውጤታማነቱ የላቀ ድርሻ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡ እንደ አቶ ከድር ገለጻ ኢንዱስትሪው በአሁኑ ወቅት ካፒታሉን ወደ 9 ሚሊዮን ብር ያሳደገ ሲሆን ለ107 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ችሏል። የኦሱ ማሽነሪ ፈጠራዎች ድርጅት ሥራ አስኪያጅ ወጣት በረከት ሀይሉ በበኩሉ ከተማ አስተዳደሩ ኢንዱስትሪዎችን ማበረታታቱ የማህበረሰቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ የተለያዩ ማሽኖችን በማምረት ለገበያ እንዲያቀርቡ ያገዛቸው መሆኑን ተናግሯል። በዚህም ድርጅቱ ካፒታሉን እያሳደገ ከመምጣቱ ባለፈ ለ15 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ጠቅሰዋል። በመንግስት በኩል የቀረበላቸው የመስሪያና የመሸጫ ቦታ እንዲሁም አስተማማኝ የሀይል አቅርቦት መኖሩ ስራቸውን ውጤታማ ማድረጉንም ተናግረዋል። ይህም ድርጅቱ ከውጭ የሚገቡ ማሽኖችን በማምረት በአነስተኛ ዋጋና በላቀ ጥራት ለገበያ ለማቅረብ አንዳስቻለው ጠቁመዋል። የህብረተሰቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ባህል እየጎለበተ መምጣቱም ሥራቸውን ለማሳደግ ብርታት እንደሆናቸው ገልጿል።
በአፋር ክልል የተገነቡ የጠጠር መንገዶችና የብረት ድልድይ ፕሮጀክቶች ተመርቀው አገልግሎት መስጠት ጀመሩ
May 20, 2026 95
ሰመራ፣ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦በአፋር ክልል በተለያዩ ዞኖችና ወረዳዎች መካከል ያለውን የትራንስፖርት ትስስር ይበልጥ ለማጠናከርና የማህበረሰቡን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል ታስበው የተገነቡ የጠጠር መንገዶችና የብረት ድልድይ ፕሮጀክቶች ተመርቀው በይፋ ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ። ፕሮጀክቶቹን መርቀው ወደ ስራ ያስገቡት የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባና የመስኖና ቆላማ አካቢዎች ሚኒስትር አብረሃም በላይ (ዶ/ር) ናቸው። በዛሬው ዕለት ከተመረቁት የልማት ፕሮጀክቶች መካከል የብረት ድልድዩን በውስጡ የያዘው የገቢ እና የኸሪ ራሱ ዞኖችን በዘላቂነት የሚያስተሳስረው የ64 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የመንገድ ፕሮጀክት አንዱ ነው። ይህ የተመረቀው የመንገድ መሠረተ-ልማት በሁለቱ ዞኖች መካከል ያለውን ትስስር ከማጠናከሩ ባለፈ፣በመካከላቸው የሚገኙትን የገለአሉ እና የሰሙሮቢ ወረዳዎችን በቅርበት የሚያገናኝና የማህበረሰቡን የትራንስፖርት ችግር በከፍተኛ ደረጃ የሚያቃልል መሆኑ ተመላክቷል። የጠጠር መንገዱና የብረት ድልድዩ 361 ሚሊዮን ብር የወጣበት ሲሆን ከ81 ሺህ በላይ ማህበረሰብን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑም ተመላክቷል። የሀደለኤላ እና ሰሙሮቢ ወረዳዎችን የሚያስተሳስረውና ከ16 ሺህ በላይ ዜጎችን ከወረዳና ከዞን ማዕከላት ጋር የሚያገናኘው የ18 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ፕሮጀክትም ሌላኛው ነው። አዲስ ለተመረቀው የ18 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ፕሮጀክት 72 ሚሊዮን ብር በጀት የወጣ ሲሆን፤ በአጠቃላይ ለልማት ሥራዎቹ 433 ሚሊዮን ብር በመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስቴር የቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አማካኝነት ወጪ መደረጉ ተጠቅሷል።
በከንቲባ አዳነች አቤቤ የተመራ ልዑክ በአዘርባጃን የተቀናጀ የከተማ ልማት ፕሮጀክትን ጎበኘ
May 20, 2026 143
አዲስ አበባ፤ግንቦት 12 /2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የተመራ የልዑካን ቡድን በአዘርባጃን ያለውን የተቀናጀ የከተማ ልማት ፕሮጀክት ጎብኝቷል። ከንቲባዋ በመልዕክታቸው፤ አዘርባጃን በአሁኑ ወቅት ካስመዘገበችው ከፍተኛ ዕድገት ጎን ለጎን የከተማ መልሶ ማልማት ሥራዎችን አጠናክራ መቀጠሏን ገልጸዋል። አሮጌ መንደሮችን በማንሳት የማደስ እንዲሁም ከዚህ ቀደም ጥቅም ላይ ያልዋሉ ቦታዎችን ለይቶ የማልማት ስትራቴጂ እየተከተለች እንደሚገኝ አመልክተዋል። በዚህም በ16 ዓመታት ጊዜ ውስጥ የሚጠናቀቁ 50 ሺህ መኖሪያ ቤቶች፣ ሆቴሎችና ተያያዥ የልማት ሥራዎች በ"Sea Breeze ፕሮጀክት" ሥር በስፋት እየተገነቡ እንደሚገኙና የግሉ ዘርፍም ከመንግሥት ጋር በመቀናጀት በከፍተኛ ደረጃ እየተሳተፈ መሆኑንም ነው ያነሱት። በአዲስ አበባም፣ በየዓመቱ 100 ሺህ ቤቶችን እና ተያያዥ ልማቶችን ለመገንባት ታቅዶ በከፍተኛ ርብርብ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ከተማ አስተዳደሩ ያረጁና የተጎሳቀሉ አካባቢዎችን የመቀየርና የማደስ ሥራዎችን እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ቀደም ሲል በአግባቡ ጥቅም ላይ ያልዋሉ እንደ የጫካ ፕሮጀክት፣ ገላን-ጉራ፣ መሐመድያ መንደር እና አዲስ ቱሞሮ ያሉ አካባቢዎችን በመጠቀም አዲስ ከተማ የመገንባት ያህል ምቹ የልማትና የመኖሪያ ስፍራዎችን ለመፍጠር እየተሠራ መሆኑን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ይህ መጠነ-ሰፊ የቤት ልማትና የከተማ ማደስ እንቅስቃሴ በዋናነት የመኖሪያ ቤት ችግርን ለማቃለልና መዲናዋን የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ የታለመ ነው ብለዋል ከንቲባዋ። በቀጣይነትም በላቀ ጥረትና በልማት ልኅቀት አዲስ አበባን እንደ ስሟ አበባ በማድረግ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ግንባር-ቀደም ለማድረግ አበክሮ የመሥራት ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አመልክተዋል።
በጋምቤላ ክልል በካሳቫና ሌሎች አዋጭ የግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፎች የተጀመሩት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
May 20, 2026 271
ጋምቤላ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ) ፡-በጋምቤላ ክልል በካሳቫና በሌሎች አዋጭ የግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፎች የተጀመሩት ተስፋ ሰጪ ስራዎች ይበልጥ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን አስታወቀ። የጋምቤላ ክልል እጅግ ሰፊና ሊታረስ የሚችል ለም መሬት፣ አመቺ የአየር ንብረት እንዲሁም ከፍተኛ ውሃ ያለው በመሆኑ ለግብርና ኢንቨስትመንት ምቹ ነው። በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በክልሉ በስፋት እየተለመደ የመጣው የካሳቫ ምርት፣ ድርቅን የመቋቋም አቅሙ ከፍተኛ በመሆኑና ለምግብ ዋስትና ከመዋሉ ባለፈ ለኢንዱስትሪ ግብዓትነት ሰፊ ፍላጎት ስላለው በክልሉ ትኩረት ከተሰጣቸው የሰብል ዓይነቶች መካከል አንዱ ነው። ክልሉ ይህንን እምቅ አቅም በመጠቀም የሃገር ውስጥና የውጭ ኢንቨስተሮችን ለመሳብ የጸጥታ ሁኔታን ከማስተካከል ባለፈ የውስጥ ለውስጥ መንገድ፣ የኤሌክትሪክና ሌሎች መሰረተ-ልማቶችን በማስፋፋት ለባለሃብቶች ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እየሰራ ይገኛል። የጋምቤላ ክልል ኢንቨስትመንት ኮሚሽን እንደገለጸው በክልሉ በባለሃብቶች የተጀመረውን ዘመናዊ የካሳቫ ልማት ወደ አርሶ አደሮች በማስፋት የምግብ ዋስትናን የማረጋገጡ ተግባር ተጠናክሮ ቀጥሏል። የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ሎው ኦቡፕ(ዶ/ር) እንዳሉት ካሳቫን ጨምሮ ለምግብ ፍጆታም ሆኑ ለገበያ አዋጭ የግብርና ኢንቨስትመንት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። የክልሉ ህዝብ ቀደም ሲል የካሳቫን ተክል እያመረተ በባህላዊ መንገድ ለምግብነት ሲጠቀም መቆየቱን አስታውሰው፤ አሁን ላይ በዘርፉ ባለሃብቶችን በማሳተፍ የካሳቫ ልማቱን ለማዘመን እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ካሳቫ ከሌሎች ስራ ስር አትክልቶች ሁሉ በምርታማነቱ ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ ተክሉ ለእንጀራና ለዳቦ ዝግጅት ከመዋሉ ባለፈ፣ ለተለያዩ የምግብ ዓይነቶች የሚያገለግል ሰብል መሆኑን ገልጸዋል። የካሳቫ ልማት በተለይም እንደ ሀገር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ለተያዘው ብሄራዊ ግብ መሳካት ዓይነተኛ ፋይዳ እንዳለውም ኮሚሽነር ሎው (ዶ/ር) ገልጸዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አቶ አንድሮው ቱት በበኩላቸው የካሳቫ ልማት በክልሉ በሚገኙ ዞኖች በባህላዊ መንገድ ሲከወን መቆየቱን ተናግረዋል። አሁን ላይ በዘመናዊ መልኩ በባለሃብት የተጀመረውን የካሳሻ ልማት ወደ አርሶ አደሩ በማስፋት እንደ ሀገር የምግብ ሎዓላዊነትን ለማረጋገጥ የታዘውን ግብ ለማሳካት በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በአቦቦ ወረዳ በካሳቫ ኢንቨስትመንት የተሰማራው የአያል ኃላፊነቱ የተወሰነ እርሻ ልማት ድርጅት ተወካይ አቶ ቾቤ ሞላ በሰጡት አስተያየት የካሳቫ ልማት በምርታማነትም ሆነ በገበያ አዋጭ ስራ መሆኑን ገልጸዋል። ካሳቫ ድርቅን የሚቋቋምና በአንድ ሄክታር መሬት ላይ ከ150 እስከ 200 ኩንታል ምርት የሚሰጥ መሆኑን ገልጸው፤ ከአራት ወር ጀምሮ ምርት መስጠት የሚችል ተክል እንደሆነ ነው የተናገሩት። ድርጅታቸው በአሁኑ ወቅት በ50 ሄክታር ማሳ ላይ ልማቱን እያከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመው በቀጣይ ዓመት ከ200 ሄክታር በላይ መሬት ልማትና የካሳቫ ዱቄት ፋብሪካ የመክፈት እቅድ ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል። የተለያዩ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ የካሳቫ ተክል ጋምቤላን ጨምሮ በደቡብና በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ አካባቢዎች በአርሶ አደሮች አነስተኛ ማሳዎች ላይ እየተመረተ ለዘመናት ለምግብነት ሲያገለግል የቆየ ሰብል ነው።
በድሬደዋ አስተዳደር ባለፉት አስር ወራት ከ17ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል
May 20, 2026 95
ድሬደዋ፣ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፡- በድሬደዋ ባለፉት አስር ወራት ከ17ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የስራ ዕድል መፈጠሩን የአስተዳደሩ ስራና ክህሎት ቢሮ ገለፀ። ቢሮው በበጀት ዓመቱ በአነስተኛና ጥቃቅን ለተደራጁ ኢንተርፕራይዞች ከ112 ሚሊዮን ብር በላይ የገበያ ትስስር መፍጠሩንም ጠቁሟል። በቢሮው የስራ ዕድል ፈጠራና የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ሰኢድ አሊ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በበጀት ዓመቱ የስራ ዕድል ለመፍጠርና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ የተቀናጁ ስራዎች አበረታች ውጤቶች ተገኝተዋል። በአስተዳደሩ በተደረገው እንቅስቃሴም በበጀት ዓመቱ አስር ወራት ከ17ሺህ 300 በላይ ለሚሆኑ ከተለያዩ የትምህርት ተቋማት ለተመረቁ ወጣቶችና የህብረተሰብ ክፍሎች ቋሚ የስራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል። ለተገኘው ውጤት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ እየመጣ የሚገኘው እመርታ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን በመጠቆም። በተጨማሪም ግብርና፣ ኮንስትራክሽን እና የአገልግሎት ዘርፎች የስራ ዕድል የተፈጠረባቸው መስኮች መሆናቸውን አቶ ሰኢድ ገልጸዋል። በአስተዳደሩ የሚገኙ የተማሩ ወጣቶችን ጥያቄዎች ከአጋር አካላት ጋር በመቀናጀት የመመለስ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉንም አክለዋል። እንደ አቶ ሰኢድ ገለፃ ቢሮው በዘንድሮ በጀት ዓመት በስሩ በተደራጁት የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች በመታገዝ በአነስተኛና ጥቃቅን የተደራጁ ኢንተርፕራይዞች ውጤታማነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ድጋፎች አድርጓል። የብድር፣ አጫጭር የሙያና የክህሎት ስልጠና እንዲሁም ከሚመለከታቸው ሴክተሮች ጋር በመቀናጀት የመስሪያና የመሸጫ ቦታዎች ማመቻቸቱን ለአብነት ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ከ600 በላይ ለሚሆኑ ኢንተርፕራይዞች ከ112 ሚሊዮን ብር በላይ የገበያ ትስስር እንዲፈጥሩ በማድረግ የዕድገት ሽግግርን እንዲያፋጥኑ መሰራቱን አንስተዋል። በስራ ዕድል ፈጠራውም ሆነ በገበያ ትስስር ሴቶች እና አካል ጉዳተኞች ትኩረት ማግኘታቸውንም ገልጸዋል።
የኢንዱስትሪ ፓርኩ መገንባት መንግሥት ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት በተጨባጭ ያረጋገጠ ነው
May 19, 2026 592
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ መገንባት መንግሥት የኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሀገር ያለውን አበርክቶ ለማሳደግ በፖሊሲና በስትራቴጂ ከመደገፍ ባለፈ በተጨባጭ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳየበት መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል ገለጹ። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል ባሳለፍነው ሳምንት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተመርቆ የተከፈተውን የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክን ጎብኝተዋል። ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ መገንባት፤ መንግሥት የኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሀገር ያለውን አበርክቶ ለማሳደግ በፖሊሲና በስትራቴጂ ከመደገፍ ባለፈ በተጨባጭ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳየበት ነው። ፓርኩ በአምራች ዘርፉ ላይ የሚስተዋለውን የመሥሪያ ቦታ እጥረት በዘላቂነት ለመፍታት የማይተካካ ሚና አለው ብለዋል። አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች አቅማቸውን ገንብተው ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪነት እንዲሸጋገሩ ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ፓርኩ የተገነባበት ጥራትና የተሟላ መሠረተ ልማት የሀገር ውስጥ ምርትን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለማድረግ ያስችላል ሲሉ ገልፀዋል። የሀገር ውስጥ ምርትን በማሳደግ የገቢ ምርቶችን ለመተካት የሚደረገውን ጥረት ለሀገር ዘላቂ ሉዓላዊነት ትልቅ አስተዋፅኦ ይኖረዋል ብለዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እንዲህ አይነት ግዙፍ ፕሮጀክት መገንባቱ ትልቅ ልምድና ትምህርት የተገኘበት መሆኑን ጠቅሰው፤ ለሌሎች አካባቢዎችም እንደ ማዕከልና አርዓያ ሆኖ እንደሚያገለግል አስገንዝበዋል። በሁሉም አካባቢዎች ኢንዱስትሪን ለማስፋፋትና የሀገርን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ጉልህ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ታረቀኝ ቡሉልታ በበኩላቸው፤ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን የኢንዱስትሪ ንቅናቄን እንደሚያግዝ ገልጸው፤ ይህም የሀገር ውስጥ የገበያ ድርሻን በማሳደግ ለኢንዱስትሪዎች ጠንካራ መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል።