ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ባለፉት ዘጠኝ ወራት የወጪ ንግድን ጨምሮ በሁሉም ዘርፎች ከፍተኛ ውጤት ተመዝግቧል
Apr 16, 2026 325
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦የበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት የወጪ ንግድን ጨምሮ በሁሉም ዘርፎች ከፍተኛ ውጤት የተመዘገበበት ነው ሲሉ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለፁ። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ከተጠሪ ተቋማት ጋር በመሆን የ2018 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸም የግምገማ መድረክ ተካሂዷል። መድረኩ “ተወዳዳሪ የንግድ ሥርዓትና የተሳለጠ የገበያ ትስስር ለኢኮኖሚ ሽግግር” በሚል መሪ ሃሳብ ነው የተካሄደው።   የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የተቋሙ ተልዕኮ የመፈጸም አቅሙ በየጊዜው እያደገ በመምጣቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሁሉም ዘርፎች ከፍተኛ ውጤቶች ተመዝግበዋል። በዘጠኝ ወራቱ በኦንላይን ንግድ ምዝገባ፣ አዲስ ፈቃድ የማውጣት፣ የማደስ እና መሰረዝ ሥራዎች ለሁለት ነጥብ ዘጠኝ ሚሊዮን በላይ ደንበኞች ቀልጣፋ አገልግሎት መሰጠቱን ተናግረዋል። በወጪ ንግድ ረገድ ከሁሉም የንግድ ዓይነቶች ሰባት ነጥብ ሰባት ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ የተገኘ መሆኑን አብራርተዋል። የገበያ መሠረተ ልማትን በማስፋት ረገድ ገበያን ለማረጋጋት የሚረዱ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ቁጥር በአሁኑ ወቅት 2ሺህ 190 መድረሱን ተናግረዋል። ሁለተኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከላትን የማስፋት ስራ መጠናከሩን አንስተው፤ በዘጠኝ ወራት ሁለት ማዕከላት ተመርቀው ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ሌሎች ሰባት ማዕከላት በግንባታ ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በምርት ጥራትና ቁጥጥር ረገድ ተጨባጭ ለውጥ መመዝገቡን ገልፀው፤ ለሀገር ኢኮኖሚ የሚመጥኑ ደረጃዎችን የማውጣትና የማስተዳደር ሥርዓት መዘርጋቱን ተናግረዋል።   የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልሃኪም ሙሉ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የንግድ ስርዓቱን ለማዘመንና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱን ተናግረዋል። የንግድ አገልግሎቶችን በቴክኖሎጂ በመደገፍ ለተገልጋዩ ይበልጥ ተደራሽ የማድረግ ስራ በስፋት ተከናውኗል ብለዋል። ህገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን ለመቆጣጠርና ተገቢውን እርምጃ ለመውሰድ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል።   የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ እንዳለው መኮንን እንደገለጹት፤ ሀገራዊ የጥራት መሠረተ ልማት ሥርዓት ላይ ውጤታማ ስራ ተሰርቷል። ባለፉት ዘጠኝ ወራት ፋብሪካን ጨምሮ ወደ ገበያውን የሚገቡ ምርቶችን በመፈተሽና የቀረቡ ምርቶችን ጥራት በማረጋገጥ ረገድም ውጤታማ ስራ መከናወኑን ገልፀዋል።
የመደመር ዕሳቤ ውጤት የሆነው ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ለአካባቢው የብልፅግና ተስፋን ይዞ መጥቷል
Apr 16, 2026 297
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 8/2018 (ኢዜአ)፦ የመደመር ዕሳቤ ውጤት የሆነው ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ለአካባቢው የብልፅግና ተስፋን ይዞ መጥቷል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በ"ገበታ ለትውልድ" ኢኒሼቲቭ ተገንብቶ የተመረቀው የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት በዛሬው ዕለት በይፋ ሥራ ጀምሯል።   ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በማስጀመሪያ መርኃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ ፕሮጀክቱ የመደመር ዕሳቤ ውጤትና ኢትዮጵያውያን በአንድነት ከቆሙ ህልሞቻቸውን ማሳካት እንደሚችሉ ማሳያ ነው። ፕሮጀክቱ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ላገዙ የፀጥታ ኃይሎች፣ የአካባቢው አመራሮችና ለሕዝቡ ምስጋና ያቀረቡት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በተለይም ባለሀብቱ አቶ በላይነህ ክንዴ ላሳዩት አርአያነት ያለው ተግባር ከፍተኛ አድናቆት ሰጥተዋል። አቶ በላይነህ በሪዞርቱ ቅጥር ግቢ የነበረውን ጫት በሙዝ፣ በፓፓያና በቡና መተካታቸውና ለአካባቢው አርሶ አደሮችም የሙዝ ችግኝ በነጻ ማከፋፈላቸው ትልቅ ትምህርት የሚወሰድበት መሆኑን ጠቁመዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወሎ የኢትዮጵያ የአንድነትና የብዝኃነት ተምሳሌት መሆኑን ጠቅሰው፤ ​"ወሎ ማለት ኅብር ማለት ነው፤ ታሪኩ፣ ባህሉ፣ እምነቱ፣ ቋንቋው፣ ዜማው፣ ገበያው፣ መልክአ ምድሩ ኅብር ነው" ብለዋል። ሪዞርቱ ከአንኮበር፣ ላሊበላ፣ አክሱም እና ኤርታሌ ለሚጓዙ ቱሪስቶች እንደ ስበት ማዕከል ሆኖ የሚያገለግል ሲሆን፤ ሌሎች ባለሀብቶችም መሰል የቱሪስት መዳረሻዎችን እንዲያለሙ ጥሪ አቅርበዋል። አካባቢው በግብርና ምርታማነት ሊለወጥ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል።   ከቆቦ እስከ መካነ ሰላም እንዲሁም ከዋግ እስከ አጣዬ ለም መሬትና የውኃ ጸጋ መኖሩን ጠቅሰው፤ አካባቢው ወደ አትክልትና ፍራፍሬ ምርታማነት መሸጋገር እንዳለበት አሳስበዋል። ተግተን ከሠራንና ፀጋዎቻችንን ካለማን የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ጉዞን እናሳካለን ብለዋል። የልማት ውጤቶች የተመዘገቡት ሰላም በመኖሩ መሆኑን በመጥቀስ፤ የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ሰላምን አጥብቀው እንዲጠብቁ አደራ ብለዋል። እንዲሁም መጭው ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ እያንዳንዱ ዜጋ የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል።
የሳዑዲ የልማት ፈንድ ከኢትዮጵያ ጋር አጋርነቱን ለማስቀጠል ያለውን ቁርጠኝነት አረጋገጠ
Apr 16, 2026 292
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 8/2018(ኢዜአ)፦ የሳዑዲ የልማት ፈንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን አጋርነት ይበልጥ ለማጠናከር ቁርጠኝነቱን ገለጸ። ዓመታዊው የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት እና የዓለም ባንክ የፀደይ ወቅት ስብስባ በዋሺንግተን ዲሲ መካሄዱን ቀጥሏል። በገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ የተመራው የኢትዮጵያ መንግሥት ልዑክ፣ ከስብስባው ጎን ለጎን ከሳዑዲ የልማት ፈንድ (SDF) ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሱልጣን አብዱልራህማን አል-ማርሻድ ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አድርጓል። በስብሰባው ወቅት ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ እና በሳዑዲ የልማት ፈንድ መካከል ያለውን ጠንካራ እና እያደገ የመጣ አጋርነት አድንቀዋል።   ሚኒስትሩ የመንግሥትን ቀጣይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ በአጽንኦት ያነሱ ሲሆን፣ ቀጣይነት ያለው የፋይናንስ ድጋፍ የሚሹ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን የኢንቨስትመንት ዘርፎችም አብራርተዋል። ለስትራቴጂካዊ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች፣ በተለይም ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሊቀርብ የሚችል ፋይናንስን እንዲሁም የኢኮኖሚ ዕድገት እና ቀጣናዊ ትስስርን ለመደገፍ የሚደረገውን የመንገድ ትስስር ማስፋፊያን ያካተቱ ሀሳቦች በውይይቱ ላይ ተነስተዋል። ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ቅድሚያ ለምትሰጣቸው የልማት ጉዳዮች ስኬታማነት ቀጣይነት ያለው ትብብር ወሳኝ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ገልጸዋል። ሱልጣን አብዱልራህማን አል-ማርሻድ በበኩላቸው የሳዑዲ የልማት ፈንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን አጋርነት ለማጠናከር ቁርጠኛ ነው ብለዋል። ዋና ስራ አስፈጻሚው ቁልፍ የሆኑ የኢትዮጵያ የልማት ኢኒሼቲቮች ለመደገፍ ትብብሩን ይበልጥ ለማጠናከር ዝግጁ እንደሆኑ መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
ጥምረቱ ኢትዮጵያ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን የምታከናውናቸውን ውጤታማ ተግባራት መደገፉን ይቀጥላል
Apr 16, 2026 88
ሀዋሳ፤ሚያዝያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ምርታማነትን ለማረጋገጥ የምታከናውናቸው ውጤታማ ተግባራት መደገፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት (አግራ) ገለጸ። የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት (አግራ-AGRA) ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎችና ባለሙያዎች በሲዳማ ክልል የኤልቶ ገበሬዎች ህብረት ሥራ ዩኒየን የሥራ እንቅስቃሴን ዛሬ ጎብኝተዋል። አግራ አነስተኛ ማሳ ያላቸው አርሶ አደሮችን በግብዓትና በቴክኖሎጂ በመደገፍ ግብርናን ለማሳደግ እኤአ በ2006 የተመሰረተ አፍሪካ መር ተቋም ነው። አግራ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ላይ አተኩሮ የሚሰራ ሲሆን የምርጥ ዘር አቅርቦት፣ የአፈር ለምነት ማስጠበቅ፣ የገበያ ትስስርን ማመቻቸትና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ግቦችን ለማሳካት እየተንቀሳቀሰ ያለ ጥምረት ነው። የኢትዮጵያ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትርና የጥምረቱ የቦርድ ሊቀ መንበር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ በጉብኝቱ ወቅት እንዳሉት፤ ጥምረቱ ኢትዮጵያን ጨምሮ በአፍሪካ በ16 ሀገራት የግብርናውን ዘርፍ ውጤታማነት ለማረጋገጥ የሚያስችል ድጋፍ ያደርጋል።   በተለይም በኢትዮጵያ አነስተኛ ማሳ ያላቸው አርሶ አደሮች ምርታማነትን በማሳደግ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በተለያየ መንገድ እየደገፈ መሆኑንም አስታውቀዋል። የጥምረቱ ፕሬዚዳንት አሊስ ሩህዌዛ በበኩላቸው ድርጅቱ በአፍሪካ የግብርና ስርዓት ሽግግርን ለማጠናከር በተለይም አነስተኛ ማሳ ያላቸው አርሶ አደሮች ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየሰራ ነው ብለዋል።   አግራ አርሶ አደሮች ባላቸው አነስተኛ ማሳ ላይ አስፈላጊው ግብዓትና ቴክኖሎጂዎችን በማቅረብ ውጤታማ መሆን እንደሚችሉ ያምናል ያሉት ፕሬዚዳንቱ ይህም የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲፋጠን ያደርጋል፤ ውጤትም ታይቶበታል ብለዋል። በአግራ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ይኼነው ዘውዴ (ዶ/ር) ጥምረቱ ምርጥ ዘርና ሌሎች ግብዓትን ከማሳለጥ ባሻገር የገበያ ትስስር እንዲፈጠር የማድረግ እንዲሁም ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ግብርናን ለማረጋገጥ የማገዝ ስራ እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።   በዚህም ከተለያዩ አካላት ጋር በትብብር የተከናወኑ ግብርናን የማዘመን፣ ምርታማነትን የማረጋገጥና የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት የማሳደግ ጥረቶች ውጤት ማስመዝገባቸውን አንስተዋል። የሲዳማ ኤልቶ የገበሬዎች የህብረት ሥራ ዩኒየን ሥራ አስኪያጅ አቶ ሲሳይ ዮሐንስ ጥምረቱ በፈጠረው የተቀናጀ ስራ አባላቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡   በተለይም የቴክኖሎጂ አቅርቦቱ የሚጠፋውን ጊዜና ጉልበት በማዳን፣ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ገበያውን የማረጋጋት ሚና እየተጫወተ ነው ብለዋል።
የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት በአካባቢው ያለውን ልማት በከፍተኛ ደረጃ የሚያነቃቃ ነው 
Apr 16, 2026 198
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን የተገነባው የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት በአካባቢው ያለውን ልማት በከፍተኛ ደረጃ የሚያነቃቃ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከዚህ ቀደም መመረቁ ይታወቃል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በሐይቅ ከተማ በመገኘት የሎጎ ሐይቅ ሪዞርትን ዛሬ ሥራ አስጀምረዋል።   የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጭነት በክልሉ ያሉ ጸጋዎችን ወደ ተጨባጭ ልማት በመቀየር ሕዝቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው። የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀሳቦች መካከል አንዱ መሆኑን ገልጸው፤ ፕሮጀክቱ በከፍተኛ ርብርብ ለውጤት የበቃ፤ በአርአያነቱ የሚጠቀስ ነው ብለዋል። ፕሮጀክቱ የአካባቢው ነዋሪዎች፣ መንግሥትና ተቋራጮች በጋራ በመሆን ያሳኩት፤ ሕዝብን በልማት ተጠቃሚ ለማድረግ ላለን ቁርጠኝነት ማሳያ ነው ሲሉም ተናግረዋል። ወሎ የበርካታ ኃይማኖታዊ እና ታሪካዊ የቱሪስት መዳረሻዎች መገኛ ናት ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ወደ ሥራ መግባት ተጨማሪ የቱሪስት መዳረሻ በመሆን አቅም እንደሚፈጥር አብራርተዋል። ፕሮጀክቱ በአካባቢው ለሚሰሩ ሌሎች ልማቶችም ምሳሌ እንደሚሆን ጠቁመው፤ ልማቱን በከፍተኛ ደረጃ የሚያነቃቃ መሆኑን ገልጸዋል። የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ በበኩላቸው፤ ለውጡን ተከትሎ ልማቱ በሁሉም አካባቢዎች እንዲዳረስ መንግሥት የቀየሰው ሥልት ውጤት እያመጣ መሆኑን ተናግረዋል።   የሁለቱ ክልል ሕዝቦች በኢኮኖሚ እና ማህበራዊ መስኮች ዘመናትን የተሻገረ መስተጋብርና ትስስር ያላቸው መሆኑንም አንስተዋል። በአማራ ክልል እየተመዘገበ ያለው ልማት በዘላቂነት ሕዝቡን ተጠቃሚ እንዲያደርግ ሰላም ወሳኝ መሆኑን አመልክተው፤ ለዚህም በክልሉ ያለው አመራር፣ የኃይማኖት አባቶች፣ ሴቶችና ወጣቶች በጋራ መሥራት ለነገ የሚባል ጉዳይ አይደለም ብለዋል። የአፋር ክልልም በሰላም ዙሪያ ከአማራ ክልል ጋር አብሮ ለመሥራት ዝግጁ መሆኑንም አረጋግጠዋል። ባለሀብቱ አቶ በላይነህ ክንዴ በበኩላቸው፤ በሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ግንባታ ተሳትፈን የታሪክ ተካፋይ የመሆን ዕድል በማግኘታችን ጥልቅ ደስታ ተሰምቶኛል ብለዋል።   በተለያዩ አካባቢዎች የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ተግባራት ላይ በሰፊው እየተሳተፍን ነው ያሉት አቶ በላይነህ፤ በቀጣይም በልማት ዙሪያ ከመንግሥት ጋር በቅርበት ለመሥራት ቁርጠኛ ነን ሲሉ ተናግረዋል። በትብብር መሥራት ከተቻለ የማይሳካ ነገር እንደሌለ የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ማሳያ መሆኑንም አንስተዋል።
የታዳሽ ኃይል የልማት ስኬቶች የአካባቢ ደኅንነት ጥበቃ የድል ማሕተሞች ናቸው 
Apr 16, 2026 261
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል የልማት ስኬቶች የአካባቢ ደኅንነት ጥበቃን በማረጋገጥ የብልፅግናን ጉዞ የሚያፋጥኑ የድል ማሕተሞች መሆናቸውን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን ሄጦሳ ወረዳ ኢተያ አካባቢ የተገነባውን የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ በዛሬው ዕለት መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።   የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ በዚሁ ወቅት፣ ኢትዮጵያ ከውሃ፣ ከንፋስ፣ ከፀሐይ፣ ከጂኦተርማል እንዲሁም ከባዮ ጋዝና ታዳሽ ኃይል አማራጮች እምቅ አቅም እንዳላት ገልጸዋል። በዚህም እያደገ የመጣውን የኃይል ፍላጎት አስተማማኝና ቀጣይነት ባለው መልኩ ለመመለስ የሚያስችሉ ተግባራት እየተሰሩ መሆናቸውን አመላክተዋል። ዛሬ የተመረቀው የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ የዚሁ አካል መሆኑን አንስተው፤ ፕሮጅክቱ በ29 ተርባይኖች 100 ሜጋ ዋት ኃይል የማመንጨት አቅም ያለው ነው ብለዋል። ይህም ሀገሪቱ ከንፋስ ኃይል የምታገኘውን የማመንጨት አቅም ወደ 504 ሜጋ ዋት በማሳደግ ተቋሙ የኃይል ስብጥርን ለማመጣጠን የሰጠውን ትኩረት የሚያግዝ ነው ብለዋል፡፡     የፕሮጀክቱ ወደ ስራ መግባት ተደማሪ አስተማማኝ የኃይል አቅርቦት እንዲኖር የሚያስችል መሆኑን በመግለጽ፤ የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል የልማት ስኬቶች የአካባቢ ደኅንነት ጥበቃን በማፋጠን የብልፅግናን ጉዞ የሚያፋጥኑ የድል ማሕተሞች መሆናቸውን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የዴንማርክ አምባሳደር ሱን ክሮግስትራፕ በበከላቸው እንደገለጹት፤ የንፋስ ኃይል ማመንጫው ለዘላቂ ኢኮኖሚ እድገትና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ወሳኝ ነው፡፡   ኢትዮጵያና ዴንማርክ በዚህ ረገድ በጋራ እየሰሩ መሆኑን አንስተው፤ የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ይህን የሚያጠናክር ከመሆኑም ባለፈ ለቀጣይ ታዳሽ ኃይል ኢንቨስትመንት መሰረት የሚጥል መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ( ዶ/ር) አነሳሸነት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ለዓለም አርአያ የሆነ ተግባር መሆኑን አንስተዋል፡፡
ከተማ አስተዳደሩ የመኖሪያ ቤት እጥረትን ለመቅረፍ በትኩረት እየሰራ ነው
Apr 16, 2026 137
መተማ ፤ሚያዝያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦ከተማ አስተዳደሩ የማህበረሰቡ ቁልፍ ጥያቄ የሆነውን የመኖሪያ ቤት እጥረት ለመቅረፍ በትኩረት እየሰራ መሆኑን በምዕራብ ጎንደር ዞን የገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር ከተማና መሰረተ ልማት ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ የገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር ከተማና መሰረተ ልማት ጽህፈት ቤት በማህበር ተደራጅተው ሲቆጥቡ ለነበሩና መስፈርቱን ላሟሉ 580 ነዋሪዎች የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ ዛሬ ሰጥቷል፡፡ የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ታረቀኝ አለማየሁ በርክክብ ስነ-ስርዓቱ ወቅት እንደገለጹት፤ የከተማ አስተዳደሩ የማህበረሰቡ ቁልፍ ጥያቄ የሆነውን የመኖሪያ ቤት እጥረት ለመቅረፍ በትኩረት እየሰራ ይገኛል።   በዚህም በ32 ማህበራት በመደራጀት ሲቆጥቡ ለነበሩና ሌሎች መስፈርቶችን ላሟሉ 580 ነዋሪዎች የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ መስጠቱን ገልጸዋል። የከተማ አስተዳደሩ ለመኖሪያ ቤት ግንባታ የሚውል 9 ነጥብ 3 ሄክታር የሚጠጋ መሬት በማዘጋጀት ለእያንዳንዱ ሰው 160 ካሬ ሜትር ቦታ ዛሬ ማስረከብ መቻሉን አስረድተዋል። ለመሬት ካሳ ከ49 ሚሊዮን ብር በላይ በመክፈል ከ3ኛ ወገን ነጻ በማድረግ ማስረከቡን ጠቁመው እድሜያቸው ለደረሰ የልማት ተነሺ ልጆችም የቤት መስሪያ ቦታ መሰጠቱን ተናግረዋል። እያንዳንዱ የማህበር አባል በተሰጠው ቦታ ላይ በተሰጠው ጊዜ ገደብ ውስጥ ፈጥኖ ወደ ስራ በመግባትና አካባቢውን በማልማት የሚጠበቅበትን ሃላፊነት እንዲወጣም አሳስበዋል።   የገንዳውኃ ከተማ ነዋሪ አቶ ሽፈራው አለነ፤ የከተማ አስተዳደሩ የቤት መስሪያ ቦታ በመስጠት የዘመናት ጥያቄያቸውን ዛሬ እንደፈታላቸው ገልጸዋል። በተሰጣቸው ቦታ ላይ ቤት ፈጥነው በመገንባት ሃብት ለመፍጠርና አሁን ካሉበት የቤት ኪራይ ችግር ለመላቀቅ ተግተው እንደሚሰሩም ተናግረዋል። ሌላኛው የቤት መስሪያ ቦታ ተጠቃሚ የሆኑት አቶ አታለለ መርሻ በበኩላቸው፤ የብዙ ጊዜ ችግር የነበረውን የመኖሪያ ቦታ ይሰጠኝ ጥያቄ በመፈታቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል። መንግስት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ ያለውን ስራ አድንቀው በተሰጣቸው ቦታ ላይ በተባለው ጊዜ ቤት ገንብተው ለማጠናቀቅ መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል። በቦታ ርክክብ ስነ-ስርዓቱ ላይ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች፣ የማህበር አባላትና አርሶ አደሮች ተገኝተዋል።
የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ጸጋን የመለየት፣ የማልማትና ወደ ሀብት የመቀየር ትልቅ ማሳያ ነው
Apr 16, 2026 179
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 8/2018 (ኢዜአ)፦ የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ጸጋን የመለየት፣ የማልማትና ወደ ሀብት የመቀየር ትልቅ ማሳያ መሆኑንና ለወሎ የብልጽግና ተስፋ እንደሆነ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሣሽነት እና በ"ገበታ ለትውልድ" መርሐ ግብር የተገነባውን የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ዛሬ በታሪካዊቷ የሐይቅ ከተማ ተገኝተው ሥራ ያስጀመሩት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በምርቃቱ ሥነ ሥርዓት ላይ ከአካባቢው ማኅበረሰብና ከአፋር ወንድሞች ጋር በአንድነት በመገኘታቸው የተሰማቸውን ታላቅ ደስታ ገልጸዋል።   ወሎ የኅብር ምልክት መሆኗን የጠቀሱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ በዕለቱ ከአፋር ወንድሞች ጋር የታየው አብሮነት የኢትዮጵያን ውበትና ወንድማማችነት ይበልጥ የገለጠ መሆኑን አመልክተዋል። ይህ ፕሮጀክት ከግንባታው ጅማሮ እስከ ፍጻሜው የመደመር ዕሳቤ በተግባር የታየበት መሆኑን ገልጸው የመንግሥት ሐሳብ፣ የባለሀብቱ ታታሪነት እና የሕዝቡ ትጋት የተሰባጠረበት ድንቅ ውጤት መሆኑን አብራርተዋል። ፕሮጀክቱ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ሌት ተቀን ጥበቃ ላደረጉ የመከላከያ፣ የፖሊስ እና የሚሊሻ አባላት፣ እንዲሁም ለአካባቢው አመራርና ሕዝብ የላቀ ምስጋና አቅርበዋል። ባለሀብቱ አቶ በላይነህ ክንዴ ሪዞርቱን ውብ አድርገው ከመገንባት ባለፈ፣ ጫትን በምርጥ የአትክልትና ፍራፍሬ ዝርያ በመተካት ለውጥ በተግባር እንደሚመጣ ማሳየታቸውን ገልጸዋል።   በተጨማሪም ባለሀብቱ ለሐይቅ ከተማ የገነቡት ትምህርት ቤት ለትውልድ የሚተርፍ ተግባር መሆኑን በመልዕክታቸው ላይ ጠቅሰዋል። ዛሬ የታየው ልማት የሰላም ውጤት መሆኑን ያመለከቱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና ወጣቶች ሰላማቸውን አጥብቀው እንዲጠብቁ አደራ ብለዋል። በአንድነት እና በትጋት ከተሠራ ቀጣናው የዕድገትና የብልጽግና መዳረሻ መሆኑ እንደማይቀርም አጽንኦት ሰጥተዋል።
የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ውጤታማነት እያደገና የኢንቨስትመንት ፍሰት እየጨመረ ነው
Apr 16, 2026 199
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ)፦ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ውጤታማነት እያደገና የኢንቨስትመንት ፍሰት እየጨመረ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡልልታ ገለጹ። የተቀናጁ የአግሮ-ኢንዱስትሪ ፓርኮች የግብርና ምርቶች የሚሰበሰቡባቸው፣ የሚቀነባበሩባቸው፣ የታሸጉ ምርቶች ለገበያ የሚቀርቡባቸውና ወደ ውጭ ለመላክ የሚዘጋጁባቸው ማዕከላት ናቸው። ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን መተካት፣ ምርቶችን እሴት ጨምሮ ወደ ውጭ መላክ፣ የግብርና ምርትን ማዘመንና የሥራ ዕድል መፍጠር ከተቋቋሙባቸው ዓላማዎች መካከል ይጠቀሳሉ። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡልልታ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት ወደ ስራ የገቡት የይርጋለም፣ ቡልቡላ፣ ቡሬ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ውጤታማነት እያደገ እና የኢንቨስትመንት ፍሰት እየጨመረ ይገኛል። ሌሎች የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በስፋት ወደ ስራ ለማስገባት እየተሰራ ነው ብለዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ፤ የግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመር ለአገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ማዋል ለኢንዱስትሪ እድገት ዋና መሰረት ነው። አገራት ቀጣይነት ላለው ኢኮኖሚያዊ እድገትና ተወዳዳሪነት እሴት ጨምሮ የሁለተኛና የሶስተኛ ደረጃ ምርቶች መላክ ወሳኝ ነው ብለዋል። የግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመር ለአገር ውስጥና ለውጭ በማቅረብ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ጉልህ አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። በሌላ በኩል በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በተከናወኑ ውጤታማ ስራዎች ስራ አቁመው የተዘጉ ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ በማስገባትና አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች ወደ ስራ እንዲገቡ ማሰቻሉን አንስተዋል። በየዓመቱ የሚዘጋጀው ሀገር አቀፍ ኤክስፖና ባዛርም ኢንዱስትሪው የደረሰበትን ደረጃ ከማሳየትና የገበያ ትስስር ከመፍጠር አኳያ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ብለዋል።  
አዳዲስ አሰራሮችን በመጠቀም ካለማነው የበጋ መስኖ ስንዴ የተሻለ ምርት እንጠብቃለን- የተሁለደሬ ወረዳ አርሶ አደሮች
Apr 16, 2026 71
ደሴ፤ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ)፡- የምርት ማሳደጊያና አዳዲስ አሰራሮችን በመጠቀም ካለሙት የበጋ መስኖ ስንዴ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ በደቡብ ወሎ ዞን የተሁለደሬ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለፁ። በበጋው መስኖ ስንዴ ልማቱ ከተሳተፉ አርሶ አደሮች መካከል አህመድ መንገሻ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ባለፉት ዓመታት ካገኙት ጥቅም ልምድ በመውስድ በዘንድሮው በጋ ስራውን በማሳደግ አንድ ሄክታር የሚጠጋ መሬታቸውን በበጋ መስኖ ስንዴ አልምተዋል። ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማቱም ማዳበሪያና ምርጥ ዘርን በአግባቡ መጠቀማቸውንና ያልተቋረጠ የባለሙያ ድጋፍ በማግኘታቸው የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። ለአጨዳ የደረሰውን የስንዴ ሰብል በጥንቃቄ በመሰብሰብና በመውቃት ከ25 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት እየጣሩ መሆኑን አስረድተዋል። ቀደም ሲል በባህላዊ መስኖ አትክልት ለማልማት ጥረት ብናደርግም ተጠቃሚ መሆን አልቻልንም ያሉት አርሶ አደሩ አሁን ላይ በዘመናዊ መስኖ ስንዴ በማልማታችን ተጠቃሚነታችን አድጓል ብለዋል። ሌላው የወረዳው ነዋሪ አርሶ አደር ሁሴን አህመድ በበኩላቸው የዘንድሮው የበጋ መስኖ ስንዴ አቋም ከባለፉት ዓመታት የተሻለ በመሆኑ ጥሩ ምርት እንጠብቃለን ሲሉ ገልጸዋል። በግማሽ ሄክታር መሬት ላይ የዘሩትን የስንዴ ሰብል በመሰብሰብ መሬቱን ለመኸር ሰብል ልማት ለማድረስ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው በዘንድሮው የበጋ ወራት ከ27 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ በማልማት ከ900 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት በትኩረት መሰራቱን ገልጸዋል። የታቀደውን ምርት ለማግኘትም ዘመናዊ ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘርና ሌሎች ግብዓቶችን በወቅቱ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ማድረግ መቻሉን አብራርተዋል። አርሶ አደሩ የደረሰውን ሰብል በፍጥነት በመሰብሰብ ለመጪው መኸር እያደረገ ያለውን የእርሻ ዝግጅት አጠናክሮ እንዲቀጥል ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህና በአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ የተመራ የፌዴራል እና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ቡድን በደቡብ ወሎ ዞን ተሁለደሬ ወረዳ በበጋ መስኖ የለማ ስንዴን መጎብኘቱ ይታወሳል።
የዓለም ባንክ እና ጣልያን ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም ድጋፋቸውን እንደሚያጠናክሩ ገለጹ
Apr 16, 2026 233
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም ባንክ እና ጣልያን ለኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም ድጋፍ ማድረጋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታወቁ። በገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ፣ የሶስትዮሽ አጋርነትን ይበልጥ ለማሳደግ ያለመ ከፍተኛ ምክክር ከዓለም ባንክ እና ከጣልያን ልዑካን ቡድን ጋር አካሂዷል። የውይይቱ ዋነኛ ትኩረት የኢትዮጵያን ቀጣይ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም ለመደገፍ በሦስቱ ወገኖች መካከል ያለውን ትብብር ማጠናከር ነው። ሀገሪቱ ቅድሚያ ከምትሰጣቸው የልማት ጉዳዮች ጋር የተጣጣመ፣ ወቅቱን የጠበቀና አስተማማኝ የፋይናንስ ድጋፍ ማሰባሰብ በሚቻልባቸው መንገዶች ላይም መክረዋል።   የኢትዮጵያ ልዑክ በቅርቡ የተመዘገቡ የማክሮ ኢኮኖሚ ስኬቶችን ያብራራ ሲሆን፤ መንግሥት የጀመረውን የማሻሻያ እንቅስቃሴ ለማስቀጠል፣ የፋይናንስ ሥርዓትን (Fiscal Discipline) ይበልጥ ለማስጥበቅና ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ ያለውን ጽኑ አቋም በድጋሚ አረጋግጧል። በውይይቱ የልማት አጋሮች የሚያደርጉት ድጋፍ የተቀናጀ መሆን ያለው ጠቀሜታ አጽንኦት ተሰጥቶበታል። ይህም የሚደረገው ድጋፍ የሚፈለገውን ውጤት እንዲያመጣና የሀብት አጠቃቀም ውጤታማ እንዲሆን የሚያስችል እንደሆነ ተመላክቷል። የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያውን ከማገዝ ባለፈ፣ ኢትዮጵያ ተለዋዋጭና ውስብስብ የሆነውን የዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ሁኔታ ተቋቁማ እንድትሻገር የሚያስችሉ የተቀናጁ የድጋፍ ማዕቀፎች ላይ ውይይት ተካሂዷል። የጣልያን ልዑክ በበኩሉ ኢትዮጵያ ለምታደርገው የልማት ጥረት ያለውን አጋርነት በድጋሚ ያረጋገጠ ሲሆን፣ በተለይም በሁለትዮሽ ትብብር እና ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ማዕቀፎች ጋር በተጣጣመ መልኩ ድጋፉን እንደሚያጠናክር ገልጿል። በተመሳሳይ ዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም ቀጣይነት ስላለው ድጋፍ በመግለጽ፣ ውጤታማ የፋይናንስ ትብብርን ለማሳደግ ከአጋሮች ጋር በቅርበት ለመሥራት ዝግጁ መሆኑን አሳውቋል። ወቅታዊ የኢኮኖሚ ተግዳሮቶችንና የፋይናንስ ውስንነቶችን በዘላቂነት ለመወጣት ጽኑ አጋርነትና የጋራ ጥረት አስፈላጊ መሆኑንም በውይይታቸው አጽንኦት ሰጥተዋል።   ከዚህም ባሻገር ተጨባጭ የልማት ውጤቶችን ለማስመዝገብ ዘላቂ የፖሊሲ ቅንጅት፣ የተቀናጀ ተግባቦት እና የጋራ ተጠያቂነት አስፈላጊ መሆናቸው በውይይቱ ወቅት ተመልክቷል። በሦስቱ ወገኖች መካከል ያለውን ጥምረት ይበልጥ ለማጠናከርና የተቀናጀ የትብብር ማዕቀፍን ለማዘጋጀት የሚደረገውን ጥረት ለማሳለጥ በውይይቱ የጋራ ስምምነት ላይ ተደርሷል። ኢትዮጵያ ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ የኢኮኖሚ ጥንካሬና ዕድገትን ለማረጋገጥ ወሳኝ የሆኑ መዋቅራዊ ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ለማድረግ ያላትን ጽኑ አቋም በድጋሚ ማረጋገጧን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
በሸገር ከተማ የህብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የበለጠ ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት ተገኝቷል
Apr 16, 2026 64
ሚያዝያ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በሸገር ከተማ የህብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የበለጠ ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት መገኘቱን የከተማው አስተዳደር አስታወቀ። በሸገር ከተማ ያለውን የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን አስመልክቶ የመስክ ምልከታ እየተካሄደ ነው። በመስክ ምልከታው ላይም የሸገር ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ጉዮ ገልገሎ እንደገለፁት፤ በሸገር ከተማ የህብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የበለጠ ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት ተገኝቷል። ከተማዋ ከተመሰረተች በኋላ እየተከናወኑ ያሉ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴዎች የህብረተሰቡን ህይወት የቀየሩ ከመሆናቸውም በላይ ኢኮኖሚያዊ ሽግግርን እውን ከማድረግ አኳያ ውጤቶች ተመዝግበዋል። ከለውጡ በኋላ በከተማዋ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ፣ ዘመናዊ አገልግሎቶችን በማስፈን፣ ክህሎትን በማዳበር እና ሁለንተናዊ ብልጽግናን በማረጋገጥ ረገድ በተሰራው ስራ ውጤት መገኘቱን አክለዋል።   በኢንቨስትመንት ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን ከመፍታትና አገልግሎት አሰጣጥን ከማዘመን ጎን ለጎን በከተማዋ የኢንቨስትመንት አማራጮችን በምርምር በመለየት መሰራቱን አመልክተዋል። የአርሶ አደሮችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ከ ከ1 ሺህ 300 በላይ አርሶ አደሮች ክህሎታቸውን ለማጠናከር የሚያስችል ስልጠና መሰጠቱን ተናግረዋል። በዚህም መሰረት የኢንቨስትመንት እድገቱን ከተማው ከመመስረቱ በፊት ከነበረው በእጥፍ ማሳደግ መቻሉንም አስረድተዋል። ባለፉት ሶስት ዓመታት የሀገር ውስጥና የውጪ ባለሀብቶች፣ አርሶ አደሮችና ሌሎችን ጨምሮ አጠቃላይ 1 ሺህ 504 ኢንቨስትመንቶች 4 ሺህ 493 ሄክታር መሬትን ማልማት ችለዋል ብለዋል።  
በሲዳማ ክልል በቴክኖሎጂ በመታገዘ ገቢን በአግባቡ ለመሰብሰብ ተችሏል - ባለስልጣኑ
Apr 16, 2026 78
ሀዋሳ፤ ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል በቴክኖሎጂ በመታገዘ ገቢን በአግባቡ ለመሰብሰብ መቻሉን የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን አስታወቀ። የባለስልጣኑ ምክትል ዳይሬክተርና የደንበኞች አገልግሎት፣ የታክስ አወሳሰንና አሰባሰብ ዘርፍ ኃላፊ ሙላት ዮሴፍ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤ በክልሉ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱን በማዘመን ውጤታማ ስራዎችን ለመስራት እየተቻለ ነው። የክልሉን ገቢ ለማሳደግ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ ሲሆን ዘመናዊ የአከፋፈል ስርዓት (የኢ-ፋይልንግና የኢ-ፔይመንት) አሰራር መዘርጋቱ ለውጤቱ አስተዋጽኦ ከማድረግ ባለፈ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት አስችሏል ነው ያሉት። በተለይም ከእጅ ንክኪ ነጻ የሆነ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱን በማዘመን ክልሉ የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ ለመሰብሰብ አስችሏል ብለዋል። በተለይም ከፍተኛ ግብር ከፋይ የሆኑ ከ626 በላይ የመንግስትና የግል ተቋማት ሙሉ በሙሉ ግብራቸውን የሚያሳውቁበትና የሚከፍሉበት የኤሌክትሮኒክስ አሰራር ነው የተዘረጋው ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመት ለመሰብሰብ ከታቀደው ከ 21 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ውስጥ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ15 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለማግኝት መቻሉን ገልፀዋል። የተሰበሰበው ገቢ የእቅዱን 94 በመቶ ለማሳካት ያስቻለ ሲሆን ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ 5 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው ገልጸዋል፡፡ ገቢው ከመደበኛና ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች የተሰበሰበ መሆኑንም ተናግረዋል። በፌዴራል ደረጃ የተሻሻለው አዲሱን የግብር አዋጅ ጨምሮ ሌሎች የታሪፍ ማሻሻያዎች መደረጋቸው የገቢ አቅምን ለማሳደግ የራሱ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ብለዋል፡፡ በዚሁ ወቅት የቁጥጥርና የአሰራር ስርዓትን በማጠናከር ለታክስ ህግ ተገዥ ባልሆኑ ከ400 በላይ ግብር ከፋዮችን ጨምሮ በክልሉ ሰባት ከተሞች ደረሰኝ ሳይቆርጡ በሚሰሩ ተቋማት ላይ እርምጃ መወሰዱን ተናግረዋል፡፡ በቀሪ ጊዜትም የተቀመጠውን እቅድ ለማሳካት ወቅታዊ ሁኔታን ያገናዘበ የክትትልና የቁጥጥር ስራ እንደሚከናወን ገልጸዋል፡፡   በሃዋሳ ከተማ ግብር ከፋይ የሆኑት መምህር ተስፋዬ አበበ፤ በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብር አከፋፈል ስርዓት መኖሩ ሂደቱን ቀልጣፋ እንዳደረገው ገልፀዋል። ግብርን በታማኝነት መክፈል ሀገራዊ ግዴታ በመሆኑ ኃላፊነታቸውን በተገቢው እየተወጡ መሆኑን አመልክተው ድርጅታቸው ላለፉት ተከታታይ ዓመታት የክልሉ ከፍተኛ ግብር ከፋይ በመሆን ሽልማት ማግኘቱን ተናግረዋል።  
በአርሲ ዞን እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ይጠናከራሉ
Apr 16, 2026 174
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች የበለጠ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።   የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ የለውጡ መንግሥት የህዝቡን ኑሮ በመሰረታዊነት የሚያሻሽሉ ውጤታማ የልማት ስራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል። አርሲ ዞንም በክልሉ ትልቅ የመልማት አቅም ያለው ዞን መሆኑን ጠቅሰው፥በአካባቢው ሰፋፊ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል። በተለይም የዞኑ አርሶ አደር አዳዲስ ኢኒሼቲቮችን ፈጥኖ በመተግበር ለሌሎችም ተሞክሮ እስከ መስጠት የደረሰ በመሆኑ ሊመሰገን ይገባል ብለዋል። የክልሉ መንግሥት የአካባቢውን ልማት የሚያፋጥኑ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎችን በልዩ ትኩረት ሲያከናውን መቆየቱንም ገልጸዋል። በተለይም የመንገድ ተደራሽነትን እና ሽፋንን ለማሳደግ ነባር የመንገድ ግንባታዎችን ከማጠናቀቅ ባለፈ፣ የአዳዲስ አገናኝ መንገዶች ግንባታ መከናወኑን ተናግረዋል። በጤናው ዘርፍም በርካታ ሆስፒታሎች ተገንብተው ወደ ስራ መግባታቸውን አውስተው፤ የንጹህ መጠጥ ውሃ ግንባታ እና የመስኖ መሰረተ ልማት ዝርጋታ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቁመዋል። እነዚህ የህዝቡን ኑሮ መለወጥ ያስቻሉ ስራዎች የበለጠ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸው፤ ለዚህ ስኬታማነትም ሁሉም አመራር በቁርጠኝነት መስራት እንዳለበት አስገንዝበዋል። ዛሬ የተመረቀው የንፋስ ኃይል ማመንጫም የአካባቢውን ልማት ለማፋጠን ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል። የዞኑ ህዝብ ያገኘውን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ድህነት እና ኋላ ቀርነትን ለማስወገድ መረባረብ እንዳለበትም ነው ያነሱት። ከዚህም ባለፈ ህዝቡ ያገኘውን ሀብት በመቆጠብ ወደ ኢንቨስትመንት ዘርፍ በማሸጋገር ራሱን በዘላቂነት መለወጥ እንዳለበት አሳስበዋል።  
የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ለአፍታም የሚቆም አይደለም-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 16, 2026 148
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ለአፍታም የሚቆም አይደለም ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን ሄጦሳ ወረዳ ኢተያ አካባቢ የተገነባውን የአሠላ የነፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ፣የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ፣በኢትዮጵያ የዴንማርክ አምባሳደር ሱን ክሮግስትራፕን ጨምሮ የፌዴራልና የክልል መንግስታት የሥራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ የአርሲና አካባቢው ህዝብ ተግቶ በመስራት የሚታወቅና ትርፍ አምራች አካባቢ ነው ብለዋል። ስንዴና ገብስን በከፍተኛ መጠንና ጥራት እንደሚያመርት ገልጸው፤በተጨማሪም አካባቢው በነፋስና ጂኦ ተርማል የታዳሽ ኃይል አማራጮች ለኢትዮጵያ የዕድገት አቅም እንዳለው አብራርተዋል። ከለውጡ በፊት የነበረው 4 ሺህ ሜጋ ዋት የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አቅም አሁን ላይ ወደ 10ሺ ሜጋ ዋት ዕድገት በማስመዝገብ ከ75 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ የማመንጨት አቅም መገንባቱን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የተደረገው ተቋማዊ የሪፎርም እርምጃም ተቋሙ ከተዘፈቀበት የዕዳ ጫና በማላቀቅ ወደ ትርፋማነት እንዲሸጋገር ማድረጉን አስረድተዋል። ይህም በተቋማት የፕሮጀክት ግንባታ የገንዘብ በጀት ለታለመለት ዓላማ በማዋል አበረታች ውጤት እየተገኘ መሆኑን እንደሚያመለክት አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ለውጥ ሕዳሴና ገናሌ ዳዋን በውሃ እንዲሁም አይሻና አሰላን በነፋስ ኃይል ማመነጫዎች ለምረቃ ማብቃት መጀመር ብቻ ሳይሆን ፕሮጀክትን በብቃት የማጠናቀቅ ልምምድ እንዲጎለብት አድርጓል ብለዋል። በዴንማርክ መንግስት የብድርና ድጋፍ በ145 ሚሊዮን ዩሮ ተገንብቶ የተጠናቀቀው የአሰላ ነፋስ ኃይል ማመንጫ ጣቢያም በሁለት ዓመታት ውስጥ ዕዳውን መመለስ የሚችል አቅም እንዳለው አንስተዋል። ኢትዮጵያ በብድር የምትወስደውን ገንዘብ ለታለመለት ዓላማ ማዋል ካልተቻለ ለትውልድ ዕዳን ያሸጋግራል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፤ የአሰላ ነፋስ ኃይል ጣቢያ በሁለት ዓመታት ዕዳውን የመክፈል አቅምም ለትውልድ ዕዳን ሳይሆን ምንዳን የማስተላልፍ ስኬት ነው ብለዋል። የዴንማርክ መንግስት ለፕሮጀክቱ ያደረገው የገንዘብ ብድርና ድጋፍም የልማት ትብብር አጋርነት ውጤታማነት ማሳያ መሆኑን አስረድተዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚሹ የልማት አጋሮች የሚሰጡት የገንዘብ ድጋፍ ለታለመለት ዓላማ መዋሉን ክትትልና ድጋፍ ማድረግ እንደሚኖርባቸው ጠቅሰዋል። የአሰላ ነፋስ ኃይል ጣቢያ ግንባታም በአካባቢው የነበረውን የመንገድ መሠረተ ልማት ክፍተትና የእናቶችን ድካም ምላሽ በመስጠት ጭምር ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው አንስተዋል።   ፕሮጀክቱ 100 ሜጋ ዋት ንጹህ የኃይል አቅርቦት በመጨመር ወደ ዘርፈ ብዙ እና ቀጣይነት ባለው የኃይል መጻዒ ዕጣ ፈንታ ለመገንባት የምናደርገውን ጉዞ ያጠናክረዋል ብለዋል። ይህም የመንገድ መሠረተ ልማቱም የአካባቢው አርሶ አደር ምርታቸውን ለግብርና ማቀነባበሪያ ፋብሪካና ለማዕከላዊ ገበያ በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያሳድግ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ለአፍታም የሚቆም አይደለም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ የኢትዮጵያን የብልፅግና ጉዞ ለማደናቀፍ የሚሹ የውስጥና የውጭ ኃይሎችም አይሳካላቸውም ብለዋል። የተጀመረው የኢትዮጵያን የብልፅግና ጉዞ እናስቀጥላለን፥ ከልማት ውጪ ያለ አካሄድ አዋጭ አይደለም ብለዋል።
ኢትዮጵያን የማኑፋክቸሪንግ ማዕከል የማድረግ ጉዳይ ትኩረት ተሰጥቶታል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 16, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 8/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያን የማኑፋክቸሪንግ ማዕከል ለማድረግ መንግስት በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ “የሉዓላዊነት ልብ” በሚል ርዕሰ ጉዳይ ከኢቢሲ ጋር በነበራቸው ቆይታ ኢትዮጵያን የማኑፋክቸሪንግ ማዕከል ለማድረግ በሎጂስቲክስና በቴክኖሎጂ ዘርፍ ታላላቅ ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ፋይዳ ለማሳደግ መሠረታዊ የሆኑት ሎጂስቲክስ፣ ንጹህ ኤነርጂና የሰው ኃይል ክህሎት ላይ ትኩረት መደረጉንም አብራርተዋል። በተለይም የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ኢትዮጵያን የአፍሪካ የአየር ትራንስፖርት ማዕከል እንደሚያደርጋት ገልጸዋል። ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት በአየር ላይ ያለውን የትራንስፖርት የበላይነት ከማስቀጠሉም በላይ፣ ለኢንዱስትሪዎች ፈጣን ዝውውር ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥርም አመልክተዋል። ከኃይል አቅርቦት አንጻርም ሀገሪቱ በህዳሴ ግድብ፣ በኮይሻ፣ በሶላር እና በሌሎች የኢነርጂ አማራጮች ምርቶችን ለዓለም ገበያ በርካሽ ዋጋ ለማቅረብ እንደሚያስችላት ነው የተናገሩት። መንግስት ከኑክሌር ኃይል ለማምረት አቅዶ እየሰራ እንደሚገኝም አመልክተዋል። ይህም ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የማኑፋክቸሪንግ መዳረሻ እንደሚያደርጋት ነው ያነሱት። ኢትዮጵያ ያላትን የወጣት ሀብት ለመጠቀም፣ ወጣቶችን በቴክኖሎጂ የማብቃት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ። በአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ስልጠና አማካኝነት ወጣቶች ከኮዲንግና ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ጋር እንዲተዋወቁ መደረጉ፣ ቴክኖሎጂን የሚገነዘብ የተማረ የሰው ኃይል ለመፍጠር እንደሚያስችልም አብራርተዋል። ይህ የሰው ኃይል ዝግጅት ለማኑፋክቸሪንግ ማዕከልነት ወሳኝ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል። መንግስት ለኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች፣ ለኤሮስፔስ፣ ለኤሌክትሮኒክስ፣ ለሶላር እና ለኬሚካል ማምረቻ ዘርፎች ልዩ ትኩረት በመስጠት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የግል ዘርፉን ለማገዝ ሲባልም የቦንድ አሠራር እንዲቀርና ብድር ለግሉ ዘርፍ እንዲመቻች መደረጉን፣ ይህም የሀገር ውስጥ ምርታማነትን እንደሚያሳድገው አመልክተዋል።
በኦሮሚያ ክልል ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ ከማድረግ ባለፈ የተሳለጠ አገልግሎት የሚሰጥባቸው ማእከላት እየተስፋፉ ነው
Apr 16, 2026 133
ቢሾፍቱ፤ሚያዚያ /8/2018(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ ከማድረግ ባለፈ የተሳለጠ አገልግሎት የሚሰጥባቸው ማእከላት እየተስፋፉ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የከተማ ልማት ክላስተር አስተባባሪ አቶ መስፍን መላኩ ተናገሩ። አስተባባሪው በሰጡት መግለጫ የክልሉ መንግስት ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ በማድረግ አገልግሎት የሚዘምንበት እና የፈጠራ ማዕከል እንዲሆኑ በትኩረት እየሰራ መሆኑን አብራርተዋል። ከተሞች የንግድ ስፍራ ብቻ ሳይሆን የምርት ማዕከላት በማድረግ ረገድም ውጤታማ የሌማት ትሩፋት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ሰው ተኮር ስራዎችን ማዕከል በማድረግ የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ ተግባራት በውጤታማነት መቀጠላቸውን ጠቅሰው፥ በከተሞች በተለይም የመስሪያ እና የመሸጫ ሼዶች ተገንብተው ለበርካታ ዜጎች ስራ እድል ፈጥረዋል ብለዋል። በክልሉ ከተሞች በበጀት ዓመቱ እስከ ሦስተኛው ሩብ ዓመት ድረስ ከ11 ሺህ 742 በላይ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ፈቃድ ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ይህም ለ700 ሺህ ሰዎች የስራ እድል መፍጠር ማስቻሉን ጠቅሰው፥ ከለውጡ በፊት 10 ሺህ የነበረው የኢንቨስትመንት ቁጥር አሁን ላይ ከ40 ሺህ በላይ መድረሱን ጠቅሰዋል። ከብድር አቅርቦት አንጻርም ከ28 ቢሊዮን ብር በላይ ብድር የተሰጠ ሲሆን ለአጭርና ረጅም ጊዜ በተሰጡ የኢንተርፕረነርሺፕ ስልጠናዎች ከ1 ሺህ 800 በላይ ስራ ፈጣሪዎችን ማፍራት ተችሏል ብለዋል። እስካሁን በተለያዩ ከተሞች 17 የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎች መገንባታቸውንና የኮሪደር ልማት ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም 115 ኪሎ ሜትር የአስፋልት መንገድ፣ 90 ኪሎ ሜትር የብስክሌት መንገድ፣ 817 ኪሎ ሜትር የእግር መንገድ፣እና 90 የመኪና ማቆሚያዎች (ፓርኪንግ) እና 40 የህጻናት መጫወቻ ስፍራዎች በክልሉ ከተሞች መገንባታቸውን አንስተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) 100 ሜጋ ዋት ኃይል የሚያመነጨውን የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክትን መረቁ
Apr 16, 2026 105
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክትን ዛሬ መርቀው ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፥ በንፋስ ኃይል አማካኝነት ጨለማን ለመግፈፍ፣ ዐቅምን በለየ የቅድመ ጥናት እና ልዩ እቅድ ወደ ተግባር የተገባበት የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ዛሬ እውን ሆኗል ሲሉ ገልጸዋል።   ይህ ፕሮጀክት 100 ሜጋ ዋት ንጹህ የኃይል አቅርቦት በመጨመር ወደ ዘርፈ ብዙ እና ቀጣይነት ባለው የኃይል መጻዒ ዕጣ ፈንታ ለመገንባት የሚደረገውን ጉዞ እንደሚያጠናክረው አመልክተዋል። ይህም አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን ለማረጋገጥና የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት ያለውን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጥ አብነት ነው ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለዘመኑ የኃይል ዐቅም ተደማሪ የሆነውን ይህን ፕሮጀክት በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን ተገኝተው መመረቃቸውን ጠቁመዋል።   የተገኘው ውጤት መሰል ስራዎችን ለማበራከት የሚያተጋ መሆኑንም ነው የተናገሩት። በሁሉም ዘርፎች የሚመዘገበው የኢትዮጵያ የዕድገት ጉዞ ተጠናክሮ እየቀጠለ ይበልጥ እንደሚለማና ኢትዮጵያ ከምንጊዜውም በላይ ታላቅ የምትሆንበት ጊዜ ሩቅ እንዳልሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል ውጤት ተገኝቷል
Apr 16, 2026 127
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ)፦የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ምርታማነት ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል ውጤት መገኘቱን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል በኢትዮጵያ በተፈጥሮ ሀብት መመናመን እንዲሁም ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ተያይዞ የድርቅ መከሰትና ሌሎች አደጋዎች ሳቢያ ህብረተሰቡ ተጎጂ ሆኖ ቆይቷል። ይህን ታሪክ ለመቀየር መንግሥት በቁርጠኝነት በመስራት፣ግብርናን ማሻገር እንዲሁም ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ በተከናወኑ ስራዎች ውጤት መገኘቱን ጠቅሰዋል። ከለውጡ መንግሥት ስኬቶች አንዱ የበጋ ስንዴ ልማት መሆኑን ጠቁመው፤ለዘመናት በሚሊዮኖች በሚቆጠር ወጪ ከውጭ ይገባ የነበረው ስንዴ ራስን በመቻል ሀገር ውስጥ ለማምረት ተችሏል ብለዋል። የተፈጥሮ ሀብት መመናመንና የድርቅ መከሰትን በዘላቂነት ለመከላከል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን ለአብነት አንስተዋል። በዚህም የተፈጥሮ ሀብት መልሶ እንዲያገግም የሚረዱና ለምግብነት የሚውሉ ሰብሎችና እጽዋቶች መተከላቸውን ገልጸው፤ይህም ቀደም ሲል በተወሰኑ አካባቢዎች ብቻ የሚመረቱ ፍራፍሬዎች በሁሉም ቦታ እንዲመረቱ አስችሏል ብለዋል። በሌማት ትሩፋት ኢንሼቲቭ የእንስሳት ሀብትን በማልማት በዶሮ፣ ማር፣ ወተት፣ አሳ ምርትና ምርታማነት በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ መቻሉንም ተናግረዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ፥ በልማታዊ ሴፍትኔት መርሃ ግብር ተራቁተው የቆዩ አካባቢዎች አገግመው ወደ ምርታማነታቸው የተመለሱ ሲሆን፤ በአካባቢው ያሉ ነዋሪዎችም የምግብ ዋስትናቸው እንዲረጋገጥ ያስቻሉ ስኬቶች ተመዝግበዋል። የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እና የዜጎችን ተጠቃሚነት ወደ ላቀ ምዕራፍ ለማሸጋገር የደን ልማት፣የአፈር መሸርሸርን የመከላከል ሥራዎች፣ የእንስሳት መኖ አቅርቦትን ማሳደግ እንዲሁም የንብ እርባታ ሥራዎች ላይ በሰፊው እየተሰራ መሆኑንም አብራርተዋል። የውኃ ምንጮችን በመጠቀም በቂ ውኃ ማከማቸት፣ የመስኖ መሰረተ ልማት ማስፋፋት፣ የእንስሳትና የሰብል ልማት ተግባራት ላይም የሚደረገው ርብርብ ተጠናክሮ መቀጠሉን አመልክተዋል። በልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት"በሚል ኢኒሼቲቭ ከጠባቂነት የተላቀቀ አስተሳሰብ እንዲዳብር በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ለአብነትም በ2018 ዓ.ም በሁሉም ክልሎች በሴፍትኔት ሲደገፉ የቆዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ራሳቸውን መቻላቸውን ጠቅሰዋል። መሰል ውጤታማ ተሞክሮዎችን በማስፋት እንደሀገር ራስን ለመቻል የሚከናወኑ ተግባራት እንደሚጠናከርም ነው ሚኒስትር ዴኤታው ያረጋገጡት።
ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከወጪ ንግድ ከሰባት ነጥብ ሰባት ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ተገኘ
Apr 16, 2026 136
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 8/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፋት ዘጠኝ ወራት ከወጪ ንግድ ከሰባት ነጥብ ሰባት ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለፁ። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ከተጠሪ ተቋማት ጋር በመሆን የ2018 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈጻጸም የግምገማ መድረክ እያካሄደ ነው። መድረኩ “ተወዳዳሪ የንግድ ሥርዓትና የተሳለጠ የገበያ ትስስር ለኢኮኖሚ ሽግግር” በሚል መሪ ሃሳብ ነው እየተካሄደ የሚገኘው።   የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የተቋሙ ተልዕኮ የመፈጸም አቅሙ በየጊዜው እያደገ በመምጣቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሁሉም ዘርፎች አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል። በዘጠኝ ወራቱ በኦንላይን ንግድ ምዝገባ፣አዲስ ፈቃድ የማውጣት፣ የማደስ እና መሰረዝ ሥራዎች ለሁለት ነጥብ ዘጠኝ ሚሊዮን በላይ ደንበኞች ቀልጣፋ አገልግሎት መሰጠቱን ተናግረዋል። በወጪ ንግድ ረገድ ከሁሉም የንግድ ዓይነቶች ሰባት ነጥብ ሰባት ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ የተገኘ መሆኑን አብራርተዋል። የገበያ መሠረተ ልማት በማስፋት ረገድ ገበያ ለማረጋጋት የሚረዱ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ቁጥር በአሁኑ ወቅት 2ሺህ 190 መድረሱን ተናግረዋል። ሁለተኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከላትን የማስፋት ስራ መጠናከሩን አንስተው፤ በዘጠኝ ወራት ሁለት ተመርቀው ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ሌሎች ሰባት ማዕከላት በግንባታ ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በምርት ጥራትና ቁጥጥር ረገድ ተጨባጭ ለውጥ መመዝገቡን ገልፀው፤ ለሀገር ኢኮኖሚ የሚመጥኑ ደረጃዎችን የማውጣትና የማስተዳደር ሥርዓት መዘርጋቱን ገልፀዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም