ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የኩታ ገጠም የቡና ልማት ውጤት አምጥቷል 
Apr 28, 2026 14
ዲላ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በኩታ ገጠም የቡና ልማት የተገኘውን ስኬት ለማስፋፋት እየተሠራ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሠ መሥተዳድር እና የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) ገለጹ። በጌዴኦ ዞን ዲላ ዙሪያ ወረዳ በሽጋዶ ቀበሌ የአረንጓዴ ዐሻራ የቡና ችግኝ ተከላ መርሐ-ግብር ተከናውናል።   አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በአረንጓዴ ዐሻራ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የአፈር ለምነትን በማሻሻል በክልሉ የግብርና ምርታማነት አሳድገዋል። በክልሉ የተጀመረው ቡናን በኩታ ገጠም የማልማት ሥራም በቡና ጥራትና ምርታማነት ላይ ውጤት ማምጣቱን ጠቅሰው፤ ተሞክሮን ለማስፋፋት እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። ያረጀ የቡና ተክልን በተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች በመተካት ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ፤ ለውጭ ገበያ የሚቀርበውን የቡና መጠን ማሳደግ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። በተያዘው የበልግ ወቅት ከ40 ሚሊየን በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞች ተከላ እየተከናወነ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በምክትል ርዕሠ መሥተዳድር ማዕረግ የግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ናቸው።   ከዚህ ውስጥ ከ5 ነጥብ 6 ሚሊየን የሚልቀው ችግኝ በኩታ ገጠም እንደሚለማ ጠቁመው፤ የቡና ጥራትና ምርታማነትን በማሻሻል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። በተያዘው ዓመት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃሐ-ግብር ቡናና ፍራፍሬን ጨምሮ የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ከ32 ሚሊየን በላይ ችግኞች ተከላ እየተካሄደ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ናቸው። የኩታ ገጠም የቡና ልማትን ለማስፋፋት በተደረገ ጥረት፤ 2 ሺህ 700 አርሶ አደሮችን በማሳተፍ ከ1 ሺህ 200 ሔክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም መልማቱን ገልጸዋል። ዛሬ በዲላ ዙሪያ ወረዳ ሽጋዶ ቀበሌ የተካሄደው የቡና ተከላ መርሐ-ግብርም የዚሁ አካል መሆኑን ተናግረዋል። የሽጋዶ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ዓለማየሁ ገብሬ፤ በአካባቢያቸው እየሰፋ የመጣው የኩታ ገጠም የቡና ልማት ልማዳዊ የቡና ልማትን በማስቀረት ምርታማነት እያሳደገ መሆኑን አንስተዋል። ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በኩታ ገጠም በሚያለሙት መሬት ከ1 ሺህ በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን መትከላቸውንም አስረድተዋል። ከቡና በተጨማሪ በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚደርሱ ቦሌቄ፣ እንሰትና ሌሎች ሰብሎችን በመትከል ተጠቃሚ ለመሆን እየሠሩ መሆናቸውንም አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በአረንጓዴ አሻራና በታዳሽ ኃይል ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካውያን በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው
Apr 28, 2026 50
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በአረንጓዴ አሻራና በታዳሽ ኃይል ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካውያን በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ክላቨር ጋቴቴ ገለጹ። በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከአፍሪካ ሕብረት፣ ከአፍሪካ ልማት ባንክና ሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበር "የአጀንዳ 2030 እና 2063 ግቦችን ለማሳካት የተቀናጀና አሻጋሪ አካሄድ መከተል" በሚል መሪ ሐሳብ ያዘጋጀው 12ኛው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን መካሄድ ጀምሯል።   በየዓመቱ የሚካሄደው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ የአፍሪካ ሕብረትን የአጀንዳ 2030 እና 2063 የዘላቂ የልማት ግቦችን አፈፃፀም ለመገምገም ነው። የአፍሪካ ሕብረት "የምንመኛትን አፍሪካ" እውን የማድረግ ግብ ለማሳካት በመንግሥታትና በአጋር አካላት መካከል ያለውን ትብብርና ቅንጅታዊ አሠራር መገምገም ያስችላል። የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ክላቨር ጋቴቴ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ እና በኢ-ተገማች የዓለም ነባራዊ ሁኔታ ተስፋና ሥጋት እያስተናገደች ነው። በአፍሪካ ቀጣይነት ያለው፣ አካታችና ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ ለመገንባት አህጉራዊ ለውጥና ሽግግር ያስፈልጋል ብለዋል። ኢነርጂ፣ መሠረተ ልማት ማስፋፋት፣ ከተማ ከማዘመን ባለፈ በሀገራት መካከል የእሴት ትስስር መፍጠር እንደሚገባም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል ጠንካራ እርምጃ እየወሰደች መሆኑን በመግለፅ፤ ለአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 ግብ መሳካት ገንቢ ሚና አለው ብለዋል። ኢትዮጵያ የደን ሽፋኗን ለማሳደግ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን መትከሏን አስታውሰው፤ በዓለም የደን ልማት ዘርፍ ከፍተኛው ኢኒሼቲቭ መሆኑን አስታውሰዋል። በኢትዮጵያ 90 በመቶ ኃይል ከታዳሽ ኃይል የሚገኝ መሆኑን ገልጸው፤ ይህ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ወሳኝነት አለው ነው ያሉት። በአረንጓዴ አሻራ፣ በታዳሽ ኃይልና ከተማ ልማት የተመዘገቡ ስኬቶች ከኢትዮጵያ አልፎ ለሌሎች ሀገራት ዘላቂ ዕድገት ገንቢ ሚና እንደሚኖረውም ተናግረዋል። ኢኒሼቲቮቹ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋም የውኃ ደህንነትን ማረጋገጥ እንደያስችሉ ጠቁመዋል። የአፍሪካን የረጅም ጊዜ የልማት ዕቅዶች እና የአጀንዳ 2063 ግቦችን ለማሳካት ጠቃሚ መሆኑንም ገልጸዋል። አፍሪካ የአጀንዳ 2030 እና 2063 ዘላቂ ግቦችን ለመፈጸም በምታደርገው ጥረት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ENA
የታዳሽ ኃይልና የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የልማት ጉዞዎች የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥን ዕድል ፈጥረዋል
Apr 28, 2026 47
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይልና የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የልማት ጉዞዎች የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥን ዕድል መፍጠራቸውን በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ በተለያዩ የልማት መስኮች ዕድገቷን የሚያፋጥን ጉዞ ላይ የምትገኝ ሀገር መሆኗን አምባሳደሩ ለኢዜአ ተናግረዋል። በተለይም በታዳሽ ኃይልና በቴክኖሎጂ ሽግግር የምትፈጥረው አስደናቂ ዐቅም ለታዳጊ ሀገራት ጭምር ተሞክሮ የሚቀሰምበት መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይልና የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የልማት ጉዞዎችም የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥኑ ወሳኝ ዘርፎች መሆናቸውን አንስተዋል። በምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና የፈጠረችው የኃይል ትስስርም የጋራ ኢኮኖሚ ዕድገትን ለማፋጠን ትኩረት የሚሰጠው የልማት መርሐ-ግብር መሆኑን ነው ያመላከቱት። ፈረንሳይም ኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል መሠረተ ልማትን ለማስፋት በምታደርገው ጥረት አስፈላጊውን የገንዘብና የቴክኒክ ድጋፍ እንደምታደርግ አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ ለዲጂታላይዜሽን መሠረተ ልማት መስፋፋት የሰጠችው ትኩረት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ዕድገት በማሳለጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ተናግረዋል አምባሳደሩ። የዲጂታል ምርታማነት ዐቅምን የበለጠ ለማጎልበት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩትን በተቋም ደረጃ መገንባቷንም አድንቀዋል። ለዲጂታል ልማት የተሰጠው ትኩረት፤ የቴክኖሎጂ ጀማሪ ኩባንያዎችን በማበረታታት የፈጠራ ክህሎትና ተነሻስነትን እያጠናከረ መሆኑንም አንስተዋል።
ከ140 ሚሊየን ብር በላይ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብትን ከምዝበራ ማዳን ተችሏል
Apr 28, 2026 37
ቦንጋ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ140 ሚሊየን ብር በላይ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብት ከምዝበራ ማዳንና ማስመለስ መቻሉን የክልሉ ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ። የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ሙሉሰው ዘውዴ እንዳሉት፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 748 የሙስና ጥቆማዎችን በመቀበል በ97ቱ ላይ አስቸኳይ የሙስና መከላከል ሥራ ተሠርቷል። እንዲሁም 134ቱ ጥቆማዎች ለፍትሕ አካላት እንዲተላለፉ መደረጋቸውን ገልጸው፤ ሌሎች 269 የሙስና ጥቆማዎች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን ተናግረዋል። በተጨማሪም 76 መዝገቦች በሂደት ላይ እንደሚገኙ አመልክተዋል። በተከናወነ አስቸኳይ የሙስና መከላከል ሥራና የኦዲት ግኝት ከ140 ሚሊየን 742 ሺህ ብር በላይ የመንግሥትና የሕዝብ ሀብት ለማዳንና ለማስመለስ መቻሉን ለኢዜአ አረጋግጠዋል። ለማዳን ከተቻለው ገንዘብም 81 ሚሊየን 550 ሺህ ብሩ በኦዲት የተገኘ እና ቀሪው ገንዘብ በቅድመ መከላከል ለማዳን የተቻለ መሆኑን አብራርተዋል። ከገንዘብ በተጨማሪ 13 ሺህ 673 ካሬ ሜትር የከተማ ቦታ እና 1 ሺህ 380 ሔክታር የገጠር መሬት ከምዝበራ ማዳን ተችሏል ብለዋል። የሀብት ምዝገባ ሥራ ሙስናን መከላከያ አንዱ መንገድ መሆኑን አስገንዝበው፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራትየ 1 ሺህ 285 አዲስ ሠራተኞችን እና 120 ከፍተኛ አመራሮችን ሀብት የመመዝገብ ሥራ መሠራቱን ተናግረዋል።
በጭሮ ከተማ ሕገ ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመከላከል የሚያስችል ተግባር እየተከናወነ ነው
Apr 28, 2026 65
ጭሮ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ጭሮ ከተማ ሕገ ወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን ለመከላከል ጠንካራ የቁጥጥር ሥራ በቅንጅት እየተከናወነ መሆኑን የከተማው የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ንግድ ጽሕፈት ቤት ገለፀ። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ተወካይ አደም ዩሱፍ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በከተማዋ የንግድ ሥርዓቱን ቀልጣፋና ሕጋዊነቱን ለማረጋገጥ ከሕብረተሰቡ ጋር በመቀናጀትና ግብረ ኃይል በማቋቋም እየተሠራ ነው። በዚህም ያለ ንግድ ፈቃድ በሚሠሩና አሳማኝ ባልሆነ መንገድ ዋጋ በመጨመር ሕብረተሰቡን በሚያማርሩ አካላት ላይ ሕጋዊ እርመጃ መወሰዱን ገልጸዋል። ለአብነትም ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሸቀጦች ላይ ያለአግባብ ዋጋ የጨመሩ፣ የሸቀጥ ዋጋን በግልፅ ቦታ ያልለጠፉ እና ጊዜ ያለፈባቸው ምርቶችን ሲሸጡ የተገኙ 141 ግለሰቦች በእስራትና በገንዘብ መቀጣታቸውን ጠቅሰዋል። የንግድ ሥርዓቱን ለማዘመን በተከናወኑ ተግባራት 748 ግለሰቦች ወደ ሕጋዊ ሥርዓቱ እንዲገቡ መደረጉን አመልክተዋል። የምዕራብ ሐረርጌ ዞን ንግድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ተወካይ ጀማል ቃሲም በበኩላቸው፤ በዞኑ 15 ወረዳዎችና አምስት ከተሞች የተለያዩ አካላትን ያሳተፈ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ሕገ ወጥ ንግድን ለመከላከል የተጠናከረ ቁጥጥር እየተደረገ ነው ብለዋል። ከሕብረተሰቡ አስተያየቶችን በማሰባሰብ መንግሥት ድጎማ የሚያደርግባቸው እንደ ነዳጅ፣ ስኳር እና ዘይት ያሉ ምርቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ እንዳይደረግ ጠንካራ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል።
የቅርስ ጥበቃና ዕድሳት ስኬት ዘርፉ በኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ገንቢ ሚና የሚወጣበትን ዕድል ፈጥሯል
Apr 28, 2026 58
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ የቅርስ ጥበቃና ዕድሳት ስኬት ዘርፉ በሀገር ገፅታ ግንባታና በኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ገንቢ ሚና የሚወጣበትን ዕድል መፍጠሩን የኢትዮጵያ ቅርስ ባለሥልጣን ገለጸ። የባለሥልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኤሊያስ ሽኩር ለኢዜአ እንዳሉት፤ በሀገራዊ ለውጡ ማግስት የኢትዮጵያን ቅርሶች ደኅንነት የሚያስጠብቅ መጠነ-ሰፊ የልማት ሥራ ተሠርቷል። የኢትዮጵያ ቅርስ ዕድሳት፣ ጥበቃና የልማት ሥራም ጎስቋላ ገፅታን በመላበስ የመፍረስ አደጋ ተጋርጦባቸው የነበሩ የሀገር ምልክቶችን መታደግ እንዳስቻለ ገልጸዋል። የቅርስ ዕድሳቱም የቱሪስት ፍሰትን በመጨመር ለበርካታ ዓመታት የቆዩ የነገሥታት መኖሪያና የአስተዳደር ሕንፃዎችን ይዘት በማስጠበቅ ለአገልግሎት ክፍት እንዲሆኑ መደረጉን ተናግረዋል። ተዘርፈው የነበሩ የኢትዮጵያ ጥንታውያን መጻሕፍትና ቅርሳ ቅርሶችንም ወደሀገር ቤት እንዲመለሱ በማድረግ ለጎብኝዎች ክፍት እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። በሀገራዊ ለውጡ ማግስት የአፄ ፋሲለደስ ቤተ-መንግሥታት፣ የሶፍ ዑኡመር ዋሻና የጅማ አባጅፋር ቤተ-መንግሥት፣ የጀጎል ግንብ መሰል ቅርሶች ዕድሳት እንደተደረገላቸው አብራርተዋል። የሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ ቅርሶች ዕድሳትም የቱሪዝም ዘርፉን በማነቃቃት ለኢኮኖሚ ዕድገት ገንቢ ሚና እንዲያበረክቱ እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የቅርስ ጥበቃ፣ ዕድሳትና ልማት ሥራ በሀገር ገፅታ ግንባታና በኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ገንቢ ሚና የሚወጣበትን ዕድል መፍጠሩንም አክለዋል። በተለያዩ ክልሎች በቅርስ ጥበቃና ልማት ሥራ የተገነቡ ሙዚየሞችም በግለሰቦችና ድርጅቶች እጅ የነበሩ ታሪካዊ ቅርሶች ዘላቂ ማረፊያ የሚያገኙበትን ዕድል መፍጠር እንደቻሉ አስረድተዋል። ይህም ትውልድ በታሪካዊ ቅርሶች ላይ ትምህርት የሚቀስምበትን ወሳኝ ዕድል እንደፈጠረ ጠቅሰዋል። የዲጂታል የቅርስ ጥበቃና አገልግሎትም የቅርስ ምዝገባ፣ ፈቃድ አሰጣጥ፣ ሙዚየም አገልግሎትና የክፍያ ሥርዓቱን በማዘመን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አመላክተዋል።
የጥጥ ልማት በአፋር - ትልቅ ዐቅምን ወደ ምርታማነት የመቀየር አዲስ ጥረት
Apr 28, 2026 97
ሰመራ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- የአፋር ክልል ያለውን ሰፊ የጥጥ ልማት ዐቅም ወደ ተሻለ ምርታማነት ለመቀየርና ዘርፉን በላቀ ደረጃ ለማልማት በትኩረት እየተሠራ መሆኑን ግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። በሀገሪቱ እየተተገበረ ያለው የብዝኀ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ ክልሎች በራሳቸው ፀጋ ላይ ተመስርተው እንዲለሙ ሰፊ በር ከፍቷል። ይህ ፀጋን ለይቶ የማልማት ጥረትም የክልሎችን የኢኮኖሚ ዐቅም ከማሳደጉም በላይ፤ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በተግባር እያረጋገጠ ነው። የአፋር ክልል የበርካታ የተፈጥሮ ፀጋዎች ባለቤት ቢሆንም፤ እነዚህን እምቅ ሀብቶች ወደ ተጨባጭ ልማት በመቀየር ረገድ ለረጅም ዓመታት ክፍተቶች ሲታዩ ቆይተዋል። ሆኖም አሁን ላይ እነዚህን ያልተነኩ ፀጋዎች ለሕዝብ ጥቅም ለማዋል የሚያስችሉ ተስፋ ሰጪ ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። በግብርና ሚኒስቴር የጥጥ ልማት መሪ ሥራ አስፈፃሚ ሳምሶን አሰፋ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የአፋር ክልል ጥጥን በመስኖ ማልማት የሚያስችል ዐቅም ስላለው ልማቱን ማስፋፋት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው። በዚህም ከባለሀብቶች በተጨማሪ አርብቶ አደሩና ከፊል አርሶ አደሩ በልማቱ መሰማራት እንዲችሉና ክልሉ ያለውን የመልማት ዐቅም ተግባር ላይ ለማዋል ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን አስረድተዋል። እንደ ሀገር የጥጥ ልማትን ለማስፋፋት ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተው፤ በ2017/18 የምርት ዘመን በስድስት ክልሎች 110 ሺህ ሔክታር መሬት በጥጥ መልማቱን ተናግረዋል። በዚህም 79 ሺህ ሜትሮክ ቶን የተዳመጠ ጥጥ በማምረት ለኢንዱስትሪዎች ማቅረብ መቻሉን ገልፀው፤ ተወዳዳሪ እና ጥራት ያለው ምርት ለማምረት የሚያስችሉ ተግባራት እንደሚጠናከሩ አረጋግጠዋል። የአፋር ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ያሲን ዓሊ (ኢ/ር) እንዳሉት፤ አፋር በጉልህ የሚታወቅበትን የጥጥ ሀብት መልሶ ለማልማት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። የክልሉ የጥጥ ምርት ጥራት ያለውና ለውጭ ገበያ ተወዳዳሪ መሆኑን ገልጸው፤ በዘርፉ ለመሰማራት ለሚሹ ባለሀብቶችና ለአካባቢው አርብቶ አደሮች ምቹ የሥራ ሁኔታ መፈጠሩን ተናግረዋል። በአፋር ክልል የሚገኘው ለም መሬት ካለምንም ተጨማሪ ማዳበሪያና ኬሚካል ለጥጥ ልማት ተስማሚ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የ"ኦርጋኒክ ኮተን ፕሮጀክት" አስተባባሪ መሰለ መኩሪያ ናቸው። ይህን ዐቅም ወደ ውጤት ለመቀየር እየሠሩ መሆኑን አንስተው፤ የልማቱ መጠናከር ለክልሉም ሆነ ለሀገር ይዞ የሚመጣው ጥቅም ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል። ግብርና ሚኒስቴር ከአፋር ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ጋር በመተባበር በአውሲ ረሱ ዞን የጥጥ ልማትን እንደገና ለማስፋፋት የሚያስችል የምክክር መድረክ አካሂዷል። በመድረኩም፤ በዱብቲ፣ አይሳኢታ፣ አፋምቦና ገረኒ ወረዳዎች የሚገኙ እምቅ የልማት አማራጮችን በመጠቀም በተለይም የተፈጥሮ ጥጥ ምርትን (Organic Cotton) ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በትኩረት እንደሚሠራ ተመልክቷል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን ከ16 ሺህ ለሚበልጡ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል
Apr 28, 2026 74
ገንዳ ውኃ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን የአካባቢን ጸጋ በመጠቀም 16 ሺህ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን የዞኑ ሥራና ክኅሎት መምሪያ ኃላፊ ኤፍሬም ወርቁ ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ 24 ሺህ ወጣቶችን በቋሚና በጊዜያዊ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተሠሩ ሥራዎች 16 ሺህ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ኃላፊው ለኢዜአ ተናግረዋል። የሥራ ዕድል ተጠቃሚዎች ፈጥነው ወደ ሥራ እንዲገቡም ከአጋር ድርጅቶችና ከአበዳሪ ተቋማት ጋር በመተባበር ከ225 ሚሊየን ብር በላይ ብድር መሠራጨቱን አረጋግጠዋል። በተጨማሪም ለሥራ ዕድል ተጠቃሚዎች የመሥሪያና የመሸጫ ቦታ በማመቻቸት ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። የተፈጠረው የሥራ ዕድልም ባለፈው በጀት ዓመት ከተፈጠረው ጋር ሲነጻጸር ከ2 ሺህ በላይ ብልጫ አለው ብለዋል።   የምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ ነዋሪ ወጣት ቅዱስ ተወልደ እንደገለጸው፤ ተቀጥሮ ሲሠራበት ከነበረ የግለሰብ ድርጅት ወጥቶ በቤትና በቢሮ ዕቃዎች ማምረት ዘርፍ የራሱን የሥራ ዕድል ፈጥሮ እየሠራ ነው። በቂ ብድርና ተከታታይ ድጋፍ ተደርጎልናል ያለው ወጣቱ፤ በቀጣይም ሥራውን በአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች አስደግፎ በማከናወን ተጠቃሚነቱን ይበልጥ ለማሳደግ እየሠራ መሆኑን አስታውቋል።   በመተማ ወረዳ በዘላቂ ተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ የሥራ ዘርፍ የሥራ ዕድል የተፈጠረለት ወጣት አደም ሙሀመድ በበኩሉ፤ ከሌሎች ጓደኞቹ ጋር በእጣንና ሙጫ ማምረት ሥራ ተሰማርተው ውጤታማ ሥራ እየሠሩ መሆናቸውን ገልጿል። የአካባቢያቸውን ሥነ-ምኅዳር በጠበቀ መንገድ ከሚያመርቱት የእጣን ምርት ሽያጭ ተጠቃሚ መሆን እንደጀመሩ ገልጾ፤ በእጣን ምርት አመራረትና ተያያዥ ተግባራት ዙሪያ የተደረገላቸው የዕውቀት ሽግግርም የተሻለ ተጠቃሚ እንደሚያደርጋቸው አመላክቷል።
በጅማ ከተማ በማኅበር ለተደራጁ ከ28 ሺህ በላይ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል
Apr 28, 2026 90
ጅማ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት ዘጠኝ ወራት በማኅበር ለተደራጁ ከ28 ሺህ በላይ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን የጅማ ከተማ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ክኅሎት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አብዱልሀሚድ ኑረዲን ገለጹ። የወጣቶችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የብድር አገልግሎት ማመቻቸትና የገንዘብ አያያዝ ሥልጠና እንዲሁም የመሥሪያና የመሸጫ ቦታዎች መመቻቸቱን ኃላፊው ለኢዜአ ተናግረዋል። ይህን ድጋፍ በማቅረብም በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ለ28 ሺህ 811 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን አረጋግጠዋል። ወጣቶቹ በተሰማሩባቸው የሥራ መስኮች ውጤታማ እንዲሆኑ ክትትልና ድጋፍ እየተደረገ መሆኑም ገልጸዋል። በማኅበር የተደራጁት ወጣቶች ገቢያቸውን ከማሳደግ ባለፈ የቁጠባ ባህልን በማዳበር ሽግግር የሚያደርጉበትን ዐቅም ለመፍጠር በቅንጅት መሠራቱንም አንስተዋል። ከጎደኞቿ ጋር በመደራጀት ምንጣፎችን በማምረት ሥራ ላይ መሰማራቷን የገለጸችው ሄርሜላ ስሜነህ፤ 1 ነጥብ 4 ሚሊየን ብር ብድር በመውሰድ ወደ ሥራ መግባታቸውን አስረድታለች።   ከተማ አሥተዳደሩ ያመቻቸላቸው የማምረቻ ቦታ፣ ድጋፍና ክትትል በሥራቸው ትርፋማ እንዲሆኑ እንዳገዛቸው ጠቁማ፤ ሥራቸውን የበለጠ ውጤታማ በማድረግ ወደ ኢንቨስትመንት ለመሸጋገር ከወዲሁ አቅደው እየሠሩ እንደሚገኙ ተናግራለች። አብርሀም በለጠም ከጓደኞቹ ጋር በመደራጀት የቡና መፈልፈያ ማሽኖችን እየሠሩ ለገበያ እያቀረቡ መሆናቸውን አስረድቷል።   ማሽኖችን ለገበያ በማቅረብ ገቢያቸውን ከማሳደግ ባለፈ ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም አስታውቋል። በጂብሰም እና ፋይበር ሥራ ላይ ተደራጅተው ውጤታማ በመሆን ለሌሎች ወጣቶች አርዓያ መሆናቸውን ያነሳው ደግሞ ብሩክ በቀለ ነው።   ሥራቸውንም ለማሳካት ከተማ አሥተዳደሩ የመሥሪያና የብድር አቅርቦት በማመቻቸቱ ለ12 ሰዎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን አመላክቷል።
የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር በቁጥር ከሚገለጽ የኢኮኖሚ ዕድገት ፍላጎት በላይ ሀገራዊ ሉዓላዊነትን በዘላቂነት የምናረጋግጥበት ወሳኝ ምሰሶ ነው
Apr 28, 2026 277
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር በቁጥር ከሚገለጽ የኢኮኖሚ ዕድገት ፍላጎት በላይ ሀገራዊ ሉዓላዊነትን በዘላቂነት የምናረጋግጥበት ወሳኝ ምሰሶ ነው ሲል የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለጸ። የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ባወጣው መረጃ መንግሥት የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን 'የሉዓላዊነት ልብ' አድርጎ በመቅረጽ፣ መሠረታዊ ፍላጎቶቻችንን በራሳችን አቅም በመሸፈን ከውጭ ጫና እና ጥገኝነት ነፃ የሆነ ስትራቴጂካዊ የኢኮኖሚ ነፃነት ለመገንባት በከፍተኛ ቁርጠኝነት እየተጋ ይገኛል ብሏል። የአገልግሎቱ ሙሉ መልዕክት እንደሚከተለው ቀርቧል። የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር በቁጥር ከሚገለጽ የኢኮኖሚ ዕድገት ፍላጎት በላይ ሀገራዊ ሉዓላዊነትን በዘላቂነት የምናረጋግጥበት ወሳኝ ምሶሶ ነው ። መንግሥት የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን 'የሉዓላዊነት ልብ' አድርጎ በመቅረጽ፣ መሠረታዊ ፍላጎቶቻችንን በራሳችን አቅም በመሸፈን ከውጭ ጫና እና ጥገኝነት ነፃ የሆነ ስትራቴጂካዊ የኢኮኖሚ ነፃነት ለመገንባት በከፍተኛ ቁርጠኝነት እየተጋ ይገኛል። ይህ መዋቅራዊ ሽግግር ተግዳሮቶችን ወደ ስትራቴጂካዊ ድል በመቀየር፣ የኢትዮጵያን ሉዓላዊ ልዕልና በተግባር እያረጋገጠ ነው። የጀመርነው ግዙፍ ሽግግር አሁን ላይ ወደ ላቀ የቴክኖሎጂ ባለቤትነት ምዕራፍ የተሸጋገረ ሲሆን ይህም መንግሥት ዘርፉን ወደ ላቀ የማምረት ሂደት ለማላቅ ያለውን ጠንካራ አቋም በግልጽ ያሳያል። በሐዋሳ፣ በደብረ ብርሃንና በአዲስ አበባ ወደ ሥራ የገቡት የሶላር ሴል ማምረቻ ፋብሪካዎች በዓመት ከአንድ ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘት ሀገራችን ከቀላል የፍጆታ ዕቃዎች ምርት ወደ ላቁ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ማምረት መሸጋገሯን በተግባር አረጋግጠዋል ። ይህንን ግብ በላቀ ደረጃ ለማሳካት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት አቅጣጫችን ከመሠረቱ የተቀየረ ሲሆን መንግሥት ከብዛት ወደ ስልታዊ ጥራት የሚያመራ አዲስ ፖሊሲ ነድፎ ወደ ተግባር ገብቷል። በዚህም ትኩረታችን ተራ ሼዶችን ከማብዛት ይልቅ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ፋይዳ ያላቸውንና የቴክኖሎጂ ሽግግር የሚያመጡ ስትራቴጂካዊ ኩባንያዎችን መሳብ ላይ ያነጣጠረ ነው። ይህ አዲስ አቅጣጫ ወጣቱን ትውልድ የላቀ የቴክኖሎጂ ባለቤት የሚያደርግና ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ የማኑፋክቸሪንግ ሰንሰለት ውስጥ ተወዳዳሪና የማይተካ የልማት አጋር እያደረጋት ይገኛል። ከከፍተኛ ቴክኖሎጂ ትኩረታችን ጎን ለጎን፣ የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ የኮንስትራክሽን ግብዓቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የዘርፉን የገቢ ምርት ጥገኝነት በከፍተኛ ፍጥነት እየቀነሰ ነው። እንደ ብረት ማዕድን፣ ማርብል እና ሲሊካ ያሉ ሀገራዊ ሀብቶችን ለኢንዱስትሪዎቻችን ቀጥታ ግብዓት እንዲሆኑ በማድረግ፣ "መግዛት ሳይሆን ማምረት " በሚለው አዲሱ መርሐችን የውጭ ምንዛሬን ከመታደግ ባለፈ የሀገር ውስጥ ባለሀብቶችን ዐቅም በሚገባ አጎልብተናል። ይህም ኢትዮጵያ የራሷን የከተሞችና የመሠረተ ልማት ዕድገት በራሷ የተፈጥሮ ሀብት የመገንባት አስተማማኝ ዐቅም እንድትፈጥርና በአምራች ዘርፉ ራሷን እንድትችል እያደረገ ነው። በአጠቃላይ መንግሥት ለዘረፉ የሰጠው ልዩ ቱኩረት እና የወሰዳቸው ቁልፍ ርምጃዎች በተለያዩ ምክንያቶች ተዘግተው የነበሩ ከ800 በላይ ፋብሪካዎችን ወደ ሥራ የመለሰ ሲሆን አጠቃላይ የማምረት ዐቅማችንን ወደ 67 በመቶ ከፍ አድርገውታል። የኢንዱስትሪ ዕድገትን ከስትራቴጂካዊ የፖሊሲ ማሻሻያዎች ጋር በማስተሳሰር ለረጅም ጊዜ ብልጽግና የጣልነው መሠረትም ዛሬ ፍሬ ማፍራት የጀመረ ሲሆን ኢትዮጵያ ዛሬ የቆመችበት ጽኑ መሠረት ነገን በልበ ሙሉነት እንድንቀበል የሚያስችል ብሩህ የታሪክ ምዕራፍ ነው። የኢፌዴሪ መንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
የኢትዮጵያ እና ሞዛምቢክ ግንኙነት ወደ አዲስ የትብብር ምዕራፍ ተሸጋግሯል - የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት
Apr 27, 2026 780
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ እና ሞዛምቢክ ግንኙነት ወደ አዲስ የትብብር ምዕራፍ መሸጋገሩን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። ትብብሩ የጋራ መተማመንና ዕድገት በሰነቀ ርዕይ ላይ የተመሠረተ መሆኑን ገልጿል።   ዛሬ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የሞዛምቢክ ሪፐብሊክ ፕሬዝደንት ዳንኤል ፍራንሲስኮ ቻፖ በተገኙበት፤ በወታደራዊ ሥልጠና፣ በከተማ ልማትና በቤት ግንባታ፣ በጤና፣ በሲቪል አቪዬሽን፣ በቱሪዝም እንዲሁም በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን፤ በተለይም በዲጂታል መታወቂያ እና ዲጂታል የሕዝብ መሠረተ ልማት ዘርፎች ላይ ያተኮሩ ታሪካዊ የመግባቢያ ሰነዶች መፈረማቸውን ጽሕፈት ቤቱ አመልክቷል። እነዚህ ስምምነቶች ከፖሊሲ ሰነድነት ባለፈ ለጋራ ብልጽግና ተጨባጭ መንገዶችን የሚቀይሱ መሆናቸውንም አስታውቋል።   የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ ባለበት በዚህ ወቅት፣ ሀገራችን የደረሰችበትን ልምድና እውቀት ለአፍሪካውያን ወንድሞቿ ለማካፈል ያላትን ቁርጠኝነት የምታረጋግጥ ሲሆን፤ በእንዲህ ዓይነት አጋርነቶችም በጋራ ለመማር እና ለማደግ ዝግጁ መሆኗን ጽሕፈት ቤቱ ገልጿል።
በግል ባለሀብት የሚለሙ የግብርና ስራዎች ለኢትዮጵያ የገጠር ሽግግር ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ነው- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ 
Apr 27, 2026 172
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የግል ባለሀብቶች በሶላር እና በከርሰ ምድር ውኃ በመጠቀም የሚያለሟቸው የግብርና ሥራዎች ለሀገሪቱ የገጠር ሽግግር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኝ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን የገለጹት ዛሬ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሆሞሻ ወረዳ የሚገኘውን ፍቃዱ ነመራ የተቀናጀ የእርሻ ልማትን በጎበኙበት ወቅት ነው። በዚህ እርሻ በ250 ሄክታር ላይ 27 ዓይነት የቋሚ ተክል፣ የሰብልና በፍጥነት ደራሽ የፍራፍሬ ልማት በተቀናጀ መልኩ እየተመረተ እንደሚገኝ በመልዕክታቸው ላይ አስፍረዋል። ፍቃዱ ነመራ የተቀናጀ የእርሻ ልማት በኢትዮጵያ የግሉን ዘርፍ ያሳተፈ የግብርና ሥራ እንዲስፋፋ ለሚደረገው ሥራ አንድ ማሳያ ነው ብለዋል። ይህ በግል ባለሀብት እየለማ ያለው የግብርና ሥራ እንደ ሶላር ያሉ የኃይል አማራጮችን እና የከርሰ ምድር ውኃን በመጠቀም በመስኖ በማልማት ኢትዮጵያ ለጀመረችው የግብርና ልማት እና የገጠር ሽግግር ሰፊ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ነው የገለጹት። ከተክል እና የሰብል ልማቱ ጎን ለጎንም የማር ምርት ላይ የሠጠው ትኩረት የአካባቢ እምቅ ፀጋ የመጠቀም ዕይታ በግሉ ዘርፍ እየሠረፀ መሆኑ የታየበት ነው ብለዋል። በእርሻው የዶሮ እርባታ፣ የንብ ማነብና የእንስሳት ልማት የተጀመረ ሲሆን የመኖ ዝግጅት መጀመሩም ትልቅ ተስፋን የሚሰጥ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ስኬታማ የልማት ጉዞ የዜጎችን ተጠቃሚነትና የከተማዋን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት እያረጋገጡ ነው
Apr 27, 2026 443
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ስኬታማ የልማት ጉዞ የዜጎችን ተጠቃሚነትና የከተማዋን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት እያረጋገጡ መሆኑ የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ ገለጹ። ከትናንት ሚያዚያ 18/2018 ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2018 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት ሥራ አፈፃጸም ግምገማ ተጠናቋል። በዚሁ ወቅት የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ፤ በመዲናዋ ለሀገር ውስጥና ለዓለም አቀፍ ተሞክሮ የሚሆኑ የልማት ስኬቶች ተገኝተዋል ብለዋል።   የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶችም ሕብረብሔራዊ አንድነትን በማፅናት በዜጎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ላይ ትርጉም ያለው ለውጥ ያመጡ መሆናቸውን ገልጸዋል። በኢኮኖሚ መስክም ግዙፍ ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት በመገንባት የመዲናዋን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያንፁ ውጤታማ የልማት ስኬቶች መገኘታቸውን አስረድተዋል። የአዲስ አባባ አስደናቂ የልማት ስኬቶች የኢትዮጵያ የብልፅግና ተምሳሌት ከተማ የመገንባት ዕሳቤን በተግባር ያስመሰከሩ መሆናቸውን አስገንዝበዋል። የመዲናዋ ዘርፈ ብዙ የልማት ስኬቶች የመዲናዋን ነዋሪዎች የአኗኗር ሥርዓትን በማዘመን ተጠቃሚነትን እያረጋገጡ መሆኑን አንስተዋል።
የሞዛምቢክ ሪፐብሊክ ፕሬዝደንት ዳንኤል ፍራንሲስኮ ቻፖ የብሔራዊ ቤተ-መንግሥት ሙዚየምን ጎበኙ
Apr 27, 2026 422
‎አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19 /2018(ኢዜአ)፦ የሞዛምቢክ ሪፐብሊክ ፕሬዝደንት ዳንኤል ፍራንሲስኮ ቻፖ የብሔራዊ ቤተ-መንግሥት ሙዚየምን ጎብኝተዋል። ጉብኝቱ በሙዚየሙ የተደረገ ጥልቅ የታሪክ ጉዞ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። የሞዛምቢክ ፕሬዝዳንት የሙዚየም ጉብኝት በኢትዮጵያ እያደረጉት ያለው ይፋዊ የሥራ ጉብኝት አካል እንደሆነም ጠቁሟል። ጉብኝቱ የኢትዮጵያን ነፃና ጥንታዊ ሥልጣኔ የሚያሳይ መሆኑን የገለጸው ጽሕፈት ቤቱ፤ የሀገሪቱ ታሪክና ቅርሶችም ለታማኝና ባለርዕይ አጋርነቷ ህያው ምስክሮች መሆናቸውን አመልክቷል። ኢትዮጵያ ምድረ ቀደምት መሆኗን የሚያሳዩ ታሪካዊ ቅርሶቿን ስታጋራ፣ ጥንታዊ ጥንካሬዋ ለዘመናዊውና ለውጥን ለሚያረጋግጠው አጋርነቷ መሠረት መሆኑን በድጋሚ ማረጋገጧን ጽሕፈት ቤቱ ገልጿል። ጉብኝቱ አፍሪካውያን ወንድሞቻችን ለጋራ የወደፊት ዕጣ-ፈንታ በአንድነት ለመሥራት ወደ ሁለተኛ ቤታቸው እንዲመጡ ጥሪ የሚቀርብበት መሆኑንም አመልክቷል።
አዲስ አበባን የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ ናቸው
Apr 27, 2026 354
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018(ኢዜአ)፦ አዲስ አበባን የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2018 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ ላለፉት ሁለት ቀናት ሲካሄድ ቆይቶ ዛሬ ተጠናቋል። የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብና አበባ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት በውጤታማነት መረጋገጥ ጀምረዋል። በግምገማው የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም የተታየ ሲሆን፤ በቀሪ ወራት የተጀመሩ ፕሮጀክቶችን በፍጥነትና በጥራት ማጠናቀቅ ላይ ትኩረት እንደሚደረግ ገልጸዋል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ የእቅድ አፈጻጸም ውጤታማ መሆኑን የጠቆሙት ከንቲባዋ፤ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ከተያዘው ዕቅድ ውስጥ በአጠቃላይ 96 በመቶ መፈጸም መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም በሁሉም ዘርፎች አዲስ አበባን የኢትዮጵያ የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን አብራርተዋል። በመዲናዋ የነዋሪውን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ በተለይም በሰው ተኮር ተግባራት የዜጎችን ሕይወት ከመሠረቱ የቀየሩ በርካታ ፕሮጀክቶች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም ከመኖሪያ ቤቶች ግንባታ በተጨማሪ የምገባ ማዕከላት፣ የተማሪዎች ምገባ፣ የኮሪደር ልማትና የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች ግንባታ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት ሕዝብን በማሳተፍ በተከናወኑ ተግባራት የመዲናዋን ሰላም አስተማማኝ ማድረግ መቻሉንም ነው ከንቲባዋ የገለጹት። አካባቢንና ወንዞችን ሲበክል የነበረውን የቆሻሻ አወጋገድ ሥርዓት ለማሻሻል በተደረገው ጥረት፣ ቀደም ሲል አንድ ብቻ የነበረው የቆሻሻ ማጣሪያ ባለፉት አምስት ዓመታት ወደ 43 ማደጉን ጠቁመዋል። ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነት የመጨረስ ባህል መዳበሩን ጠቅሰው፤ አዲስ አበባን የጤና ቱሪዝም ከተማ ከማድረግ አኳያ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆስፒታሎች መገንባታቸውንም ተናግረዋል። የአገልግሎት አሰጣጥን ከሌብነትና ከብልሹ አሠራር ለመከላከል በተከናወኑ ተግባራት መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሰጣጥን ማሳለጥ መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ የዋጋ ንረትን ከመከላከል አኳያም በከተማዋ የመግቢያ በሮች የገበያ ማዕከላት መገንባታቸውን ጠቅሰው፤ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች መስፋፋታቸውን ጠቁመዋል፡፡
የአፍሪካ አሕጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናን በተሟላ ሁኔታ በመተግበር የአሕጉሪቱን የማዕድን ሀብት ጥቅም ላይ ማዋል ይገባል
Apr 27, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ አሕጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናን በተሟላ ሁኔታ በመተግበር አሕጉሪቱ ያላትን ዕምቅ የማዕድን ሀብት ጥቅም ላይ ማዋል የሚያስችል ትብብር መፍጠር እንደሚገባ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ደሳለኝ ገለጹ፡፡ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከታንዛኒያ የአፍሪካ ዘላቂ ልማት አመራር ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "የአፍሪካ ወሳኝ ማዕድናትን ለአረንጓዴ የኢንዱስትሪ አብዮትና ዘላቂ ልማት ማዋል" በሚል መሪ ሃሳብ ያዘጋጁት የ12ኛውን የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ፎረም ቅድመ ጉባኤ አካሂዷል። የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የአፍሪካ ዕምቅ የማዕድን ሃብት የአህጉሪቱ ብልፅግና የማፋጠን ግዙፍ አቅም አለው። የአህጉሪቱን ሃብት በጥሬ ዕቃ ወደ ውጭ ከመላክ ይልቅ ዕሴት የታከለበት ማዕድን ማምረት የሚያስችል ኢንዱስትሪ መገንባት እንደሚገባ ገልጸዋል። አፍሪካ በዓለም አቀፍ የኢንዱስትሪ አብዮት ዘመን የመገበያያ ገንዘብ የነበሩ እንደኮባልት፣ ሊቲየም፣ መዳብ፣ ማንጋኒዝና ብርቅዬ የከርሰ ምድር ማዕድናት የታደለች መሆኗን ተናግረዋል። ማዕድናቱ በዓለም የግብይት ሰንሰለት ላይ ከፍተኛ ሚና ያላቸውና ለባትሪ፣ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪና ታዳሽ ኃይል ልማት የሚያገለግሉ መሆናቸውን አንስተዋል። በዚህም የአፍሪካን የአረንጓዴ ሽግግር በማጠናከርና የከበሩ ማዕድናትን በማልማት የአህጉሪቱን ዕምቅ የተፈጥሮ ፀጋና የድኅነት ተቃርኖ ማስታረቅ እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል። የአህጉሪቱን የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ትስስር የሚያሳልጥ መሰረተ ልማት ግንባታን በማጠናከር የኃይል ትስስርና የሎጀስቲክስ አቅም መገንባት እንደሚገባም ጠቅሰዋል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናን በተሟላ መንገድ በመተግበር የተቀናጀ አህጉራዊ የዕሴት ሰንሰለትን የሚያፋጥን የትብብር ሥርዓት መፍጠር ይገባል ብለዋል። የአህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ስምምነት ደንብና ደረጃዎችን በማጣጣም በዓለም አቀፍ የገበያ ሥርዓት የመደራደር አቅምን ማሳደግ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። በተለይም የአንድ አፍሪካ ሀገር የማዕድን ሃብት ተቆፍሮ፣ በሌላ የአፍሪካ ሀገር የሚቀነባበርበትንና በሶስተኛ የአህጉሪቱ ሀገር ምርት ሆኖ የሚወጣበትን ሁኔታ ጭምር ማሰብ እንደሚጠይቅም አብራርተዋል። የአፍሪካ ሀገራት የእርስ በዕርስ ትብብር የዓለም አቀፍ የኢንዱስትሪ ኃይል የሚሆኑበትን አቅም በመገንባት ተጠያቂነት የሰፈነበት የማዕድን ልማትና ተቋማትን መገንባት እንደሚያስችላቸው ተናግረዋል። አፍሪካ ፍትሕዊ ዓለም አቀፍ አጋር እንጂ ምፅዋት የምትሻ አህጉር አለመሆኗን ጠቁመው፤ የልማት አጋሮችም አህጉሪቱን ከጥሬ ዕቃ ምንጭነት ባሻገር የስትራቴጂክ ኢንዱስትሪ መዳረሻ በማድረግ ሊመለከቷት ይገባል ብለዋል። የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤም የአየር ንብረት ለውጥ፣ ዝቅተኛ የካርቦን ሽግግርና የማዕድን ሃብት ልማትን የሚያፋጥን አህጉራዊ ትብብርን ለማጠናከር ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረውም አንስተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ENA
ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅት አባል የመሆን ጉዞዋ ወደ ተጨባጭ ምዕራፍ ተሸጋግሯል
Apr 27, 2026 196
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅት አባል የመሆን ጉዞ ወደ ተጨባጭ ምዕራፍ መሸጋገሩን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። የዓለም ንግድ ድርጅት ሰባተኛው የኢትዮጵያ የስራ ቡድን ስብሰባ ከፍተኛ ዲፕሎማሲያዊ ድል የተመዘገበበት መሆኑን ሚኒስትሩ ጠቁመዋል። ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) የዓለም የንግድ ድርጅት አባልነት ድርድር ሂደትና በተከናወኑ ስራዎች ላይ እንዲሁም በጄኔቫ የተካሄደውን የዓለም የንግድ ድርጅት ሰባተኛው የኢትዮጵያ የስራ ቡድን ስብሰባ ዙሪያ ለመገናኛ ብዙሀን መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ በመግለጫቸውም ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅት አባል ለመሆን ከፍተኛ ስራ መስራቷን ገልጸው፤ እነዚህ ስራዎች በእውቀት እንዲሁም ብሔራዊ ጥቅምን ባስጠበቀ መንገድ እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። ከለውጡ ወዲህ ኢትዮጵያን የዓለም የንግድ ድርጅት አባል ለማድረግና ድርድሩ ባጠረ ጊዜ እንዲጠናቀቅ ውጤታማ ድርድሮች መከናወናቸውን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ያደረገችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለዓለም አቀፍ የንግድ አባልነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጉን ጠቁመው ከአባል ሀገራት ለሚቀረቡ ጥያቄዎችም የሀገርን ጥቅም ባስጠበቀ መልኩ ምላሽ መሰጠቱን ተናግረዋል። በጄኔቫ የተካሄደው የዓለም የንግድ ድርጅት ሰባተኛው የኢትዮጵያ የስራ ቡድን ስብሰባ ከፍተኛ ዲፕሎማሲያዊ ድል የተመዘገበበት መሆኑን እንዲሁም መግባባት ላይ የተደረሰበትና የሚቀርቡ ጥያቄዎችም እየቀነሱ መምጣታቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅት አባል የመሆን ጉዞ ግልጽ ወደሆነ ምዕራፍ መሸጋገሩን ጠቁመው በድርድር ሂደቱ ኢትዮጵያ ያከናወነቻቸው ስራዎች በአባላቱ እውቅና እንደተሰጠውም አንስተዋል። የዓለም የንግድ ድርጅት ስምንተኛው የኢትዮጵያ የስራ ቡድን ስብሰባ በመጪው መስከረም ወር እንደሚካሄድ አመላክተዋል።
በዞኑ በሻይ ቅጠል ልማት የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል
Apr 27, 2026 124
ጅማ ፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦በጅማ ዞን የሻይ ቅጠል ልማትን በኢኒሼቲቭ መልክ በመተግበር የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ከማሳደግ ባለፈ ለበርካቶች የስራ ዕድል እየተፈጠረ መሆኑ ተመለከተ። በዞኑ ከአንድ ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሻይ ቅጠል የማልማት ስራ መጀመሩን የዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት ገልጿል። የዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም እንዳሉት፤ በዘንድሮ ክረምት በተመረጡ ስድስት ወረዳዎች የሚተከል 50 ሚሊየን የሻይ ቅጠል ችግኝ እየተዘጋጀ ነው።   የችግኝ ተከላውን በህዝብ ተሳትፎ በማከናወን 1ሺህ 725 ሄክታር መሬት ለመሸፈን ከወዲሁ ወደ ስራ መገባቱን አስረድተዋል። የሻይ ቅጠል ልማቱን ከማስፋፋት ባለፈ የገበያ ትስስር የመፍጠርና ጥራቱን የጠበቀ ምርት ለፋብሪካ ለማቅረብ ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ መሰጠቱን ጠቅሰዋል። በዞኑ በሻይ ቅጠል ልማት ላይ እየተሳተፉ የሚገኙት አርሶ አደሮች በበኩላቸው፤ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት በሚያደርግላቸው የሙያና የተሻሻሉ ዝርያዎች ድጋፍ ተጠቃሚነታቸውን እንዳሳደገው ተናግረዋል።   በዞኑ ሻይ ልማት ላይ ከተሳተፉ አርሶ አደሮች መካከል የሰቃ ጨቆርሳ ወረዳ ነዋሪው ስራጅ ሼክ ከድር ፤ በሻይ ቅጠል ልማት ላይ መሳተፍ ከጀመሩ ሁለት አመታት ወዲህ ገቢያቸው መጨመሩን ተናግረዋል።   ወረዳው የሰጣቸውን ምርታማነታቸው የተሻሻለ የሻይ ተክልን በማልማትና የባለሙያ ድጋፍን በማግኘታቸው ተጠቃሚነታቸው እንዳደገ ጠቁመዋል። ሌላኛው የወረዳው አርሶ አደር ሱልጣን አባሞጋ፤ ከዚህ ቀደም ተሰማርተውበት በነበረው የተለያዩ የሰብል ልማቶች ተጠቃሚነታቸው አነስተኛ እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ላይ በሻይ ቅጠል ልማት ተሰማርተው ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደግ እንደቻሉ ጠቁመው ለስራቸው ስኬታማነት ሙያዊ ድጋፍ እና ክትትል በግብርና ፅህፈት ቤት ባለሙያዎች እየተደረገላቸው መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም