ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ሚኒስቴሩ በጋሞ ዞን ያስገነባውን የጸሀይ ኃይል ማመንጫ ለአገልግሎት አበቃ
Mar 30, 2026 58
አርባ ምንጭ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በጋሞ ዞን ጋርዳ ማርታ ወረዳ በ500 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባው የጸሀይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ለአገልግሎት አበቃ። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታው ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ(ዶ/ር) በምረቃው ላይ እንደገለጹት፤ ፕሮጀክቱ 710 ኪሎ ዋት ኃይል ማመንጨት የሚችል ሲሆን፣ 6 ሺህ 500 አባወራዎችን ተጠቃሚ ያደርጋል። ፕሮጀክቱ የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እንደሚያሳልጥ ጠቅሰው፤ በተለይ ለወጣቶች የሥራ ዕድል ከመፍጠር አኳያ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉን የተናገሩት ሚኒስትር ዴኤታው፣ የአካባቢው ማህበረሰብ ለተገነባው መሠረተ ልማት ተገቢውን ጥበቃ እንዲያደርግም አሳስበዋል። ለአካባቢው ማህበረሰብ የኃይል ስርጭቱን ለማዳረስ 7 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን መካከለኛ መስመር እንዲሁም 17 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ዝቅተኛ መስመር ተዘርግቷል ብለዋል። ኢትዮጵያ በውሃ፣ በፀሐይ ብርሃን፣ በነፋስና በሌሎች የታዳሽ ኃይል ምንጮች ወደ 150 ጊጋ ዋት ማመንጨት የሚያስችል አቅም ያላት ቢሆንም፤ እስካሁን ጥቅም ላይ የዋለው 9 ነጥብ 5 ጊጋ ዋት ብቻ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ጠቁመዋል። የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ደምስ አድማሱ (ዶ/ር)፤ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በጋርዳ ማርታ ወረዳ ህዝብን ተጠቃሚ ያደረገ ፕሮጀክት ገንብቶ በማስረከቡ ምስጋና አቅርበዋል። አካባቢው ከመሠረተ ልማት ርቆ በመቆየቱ ህዝቡ የኃይል ተጠቃሚ ሳይሆን መቆየቱን አስታውሰው፤ ፕሮጀክቱ መንግስት የገባውን ቃል በተግባር ያሳየበት ነው ብለዋል። በተለይ የጤና ተቋማት የላቦራቶሪ አገልግሎት እንዲሰጡ እንዲሁም የትምህርት ተቋማት ቴክኖሎጂን እንዲጠቀሙ በማስቻል ረገድ ፕሮጀክቱ ጉልህ ፋይዳ እንዳለውም ተናግረዋል።
የአፋር ክልልን የቱሪስት መዳረሻዎች የበለጠ ለማልማት እና ለማስተዋወቅ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Mar 30, 2026 154
ሰመራ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ የአፋር ክልል የቱሪስት መዳረሻዎችን የበለጠ ለማልማት እና ለማስተዋወቅ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ቱሪዝም ቢሮ ገለጸ። የአፋር ክልል ቱሪዝም ቢሮ የቱሪስት መዳረሻዎችን በማስተዋወቅና በማልማት ረገድ ከሰመራ ዩኒቨርሲቲ ጋር የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል። የክልሉ ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ ኢብራሂም ሁመድ እንደገለጹት የተደረገው ስምምነት ዘርፉን የበለጠ ለማስተዋወቅና ለማልማት ትልቅ እገዛ ያደርጋል። ስምምነቱ የአፋር ክልልን የቱሪዝም መዳረሻዎች ተወዳዳሪ ለማድረግ የሚያስችሉ በምርምር ላይ የተመሰረቱ ሥራዎችን ለማከናወንም ያግዛል ብለዋል። ቢሮው ዘርፉን የበለጠ ለማሳደግ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት የሚያጠናክሩ እንቅስቃሴዎችን እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፣ ይህም ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም በዘላቂነት ለማሳደግ የሚያስችል አሰራር ለማዘመን የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የሰመራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት መሐመድ ኡስማን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ለቀጣይ አምስት ዓመታት የሚቆየው ስምምነቱ የአፋርን ክልል ቱሪዝም ለማሳደግ ቁልፍ መሆኑን ጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው ሁሉን አቀፍ የቱሪዝም ልማት ስትራቴጂ ማዘጋጀት፣ የቱሪስት መስህብ መረጃዎችን በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዙ ማድረግ እንዲሁም ዘመናዊ የቱሪስት መዳረሻ ካርታ እና የማስተዋወቂያ ሥራዎችን ያከናውናል ብለዋል። ከዚህም ባለፈ ስምምነቱ የቱሪዝም ልማትን በምርምር ሥራዎች በመምራት ዓለም አቀፍ ደረጃውን እንዲጠብቁ ለማድረግም እንደሚያግዝ አመልክተዋል።  
የቻይና የፋይናንስ ተቋማት ለኢትዮጵያ የልማትና ኢኮኖሚ ማሻሻያ ድጋፍ ማድረጋቸውን እንደሚቀጥሉ አረጋገጡ
Mar 30, 2026 67
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ የቻይና የፋይናንስ ተቋማት ለኢትዮጵያ የልማትና የኢኮኖሚ ማሻሻያ ስራዎች የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታወቁ። በገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ የተመራ ከፍተኛ የኢትዮጵያ ልዑክ በቻይና የስራ ጉብኝት እያደረገ ነው። ልዑኩ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)፣ የገንዘብ ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችን ያካተተ ነው። በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር ተፈራ ደርበውም የተገኙ ሲሆን፤ የልዑኩ ጉብኝት ሁለት አላማዎችን ያነገበ ነው። ይህም በሂደት ላይ ያለውን የዕዳ ሽግሽግ ድርድር ማጠናቀቅ እና ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት ግንባታ የሚውል የፋይናንስ ስምምነቶችን ማፋጠን ላይ ትኩረቱን አድርጓል። ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር ያላትን የቆየ የኢኮኖሚ አጋርነትም ይበልጥ እንደሚያጠናከር ተመላክቷል። ልዑካን ቡድኑ በቆይታው ከቻይና ኤክስፖርት-ኢምፖርት ባንክ፣ ከቻይና ኢንዱስትሪና ንግድ ባንክ እና ከቻይና ልማት ባንክ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ተከታታይ ውይይቶችን አድርጓል። ውይይቶቹ የዕዳ ሽግሽግ ሂደቱን በማጠናቀቅና ለኢትዮጵያ ቅድሚያ ለሚሰጣቸው የመሠረተ ልማት ኢንቨስትመንቶች አዲስ የፋይናንስ ምንጭ ለማግኘት በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ ናቸው። የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በዕዳ ሽግሽግ ድርድሩ ላይ ከፍተኛ መሻሻል መታየቱን ገልጸው፤ ሂደቱ አሁን ላይ የማጠቃለያ ምዕራፍ ላይ መድረሱን አመልክተዋል። ይህ ሂደት በተሳካ ሁኔታ መጠናቀቅ ለመንግስት አስፈላጊውን የበጀት ነፃነት በመፍጠር፣ ሀገራዊ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎችንና ዕድገት ተኮር የልማት ተግባራትን ለማፋጠን እንደሚያስችል ተናግረዋል። የቻይና የፋይናንስ ተቋማት በበኩላቸው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር ኢትዮጵያ እያስመዘገበች ያለውን የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ውጤቶች አድንቀዋል። መንግስት በዕዳ ሽግሽግ ሂደቱ ላይ እያሳየ ያለውን ገንቢ ተሳትፎና የተመዘገበውን ስኬት በማድነቅ፣ ለኢትዮጵያ የልማትና የኢኮኖሚ ማሻሻያ ጥረት የሚያደርጉትን ድጋፍ እንደሚቀጥሉ በድጋሚ አረጋግጠዋል። በተጨማሪም ሚኒስትሩ የኢትዮጵያና የቻይናን ስትራቴጂካዊ አጋርነት ጥንካሬ በማንሳት፣ የፋይናንስ ተቋማቱ ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ የሚውለውን የፋይናንስ ማዕቀፍ የመገምገምና የማጽደቅ ሂደት እንዲያፋጥኑ ጥሪ አቅርበዋል። ፕሮጀክቱ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ፋይዳና አዋጭነት ያለው መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፣ ይህም ኢትዮጵያ በቀጣናው ያላትን የአቪዬሽን ማዕከልነት ለማጠናከርና ለረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ሽግግር ቁልፍ ሚና እንዳለው አብራርተዋል። ሁለቱ ወገኖች በመሠረተ ልማት ፋይናንስና ኢኮኖሚ አጋርነት ዙሪያ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከርም ተስማምተዋል። ይህም በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የቆየና የጋራ ተጠቃሚነትን መሠረት ያደረገ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚያሸጋግር የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
በአዲስ አበባ እና በሸገር ከተሞች አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን ማረጋገጥ የሚያስችል የመሰረተ ልማት ግንባታ እየተከናወነ ነው
Mar 30, 2026 124
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ እና በሸገር ከተሞች አስተማማኝ የኃይል አቅርቦትን ማረጋገጥ የሚያስችል ዘመናዊ የመሰረተ ልማት ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስታወቀ። በከተሞቹ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦትን አስተማማኝ ለማድረግ የዲስትሪቡሽን መስመር መልሶ ግንባታና አቅም ማሳደግ ፕሮጀክት በመከናወን ላይ ይገኛል። ፕሮጀክቱ የኃይል ማከፋፈያ ኔትወርክ ጥራትን ለማሻሻል የሚያግዙ ከኃይል ማከፋፈያ ጣቢያዎች የሚወጡ መስመሮችን መልሶ መገንባትና ማሻሻል፤ እንዲሁም ከፈቃድ በላይ የሆነ የኃይል ፍጆታን ለመቆጣጠር የሚያስችሉ 62 የሎድ ብሬክ ስዊቾችን መግጠምን ያካትታል። የሚገነቡት መስመሮች በኮንክሪት ምሰሶዎች እና በሽፍን ኬብል የሚከናወኑ በመሆናቸው ለአደጋ የማይጋለጡና ለረጅም ዓመታት አገልግሎት መስጠት የሚያስችሉ ናቸው ተብሏል። የአዲስ አበባ ዲስትሪቢውሽን ሪሃቢሊቴሽን 4ኛ ምዕራፍ ፕሮጀክት ሃላፊ ቅድስት ላቀው ለኢዜአ እንደተናገሩት ፕሮጀክቱ በዋናነት የኃይል ኔትወርክ እድሳትን እና የመስመሮችን አስተማማኝነት ማረጋገጥን ዓላማ ያደረገ ነው። በዚህም 2 ሺህ አዲስ የተለያየ አቅም ያላቸው ትራንስፎርመሮች ተከላና 2 ሺህ ነባር ትራንስፎርመሮች አቅም የማሳደግ ሥራ እንደሚከናወን ጠቁመዋል፡፡ በፊዩዝ የነበረ ትራንስፎርመር ወጪ በዲስትሪቢዩሽን ቦክስ እንደሚሆን ተናግረው ይህም የሚቆራረጡ መስመሮች በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚቀንስ ተናግረዋል። በአዲስ አበባ እና ሸገር ከተሞች 673 ኪሎሜትር የሚሆን መስመሮች እንደሚቀየሩ ገልጸው፤ ሽፋን የሌለው የኤሌክትሪክ መስመር ገመዶች እንደሚቀየሩና የኤሌክትሪክ መቆራረጥን እንደሚያስቀር ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ አስተማማኝ የሀይል አቅርቦትን ማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑንም ጠቁመዋል።   የቻይና ኢነርጂ ግሩፕ ምክትል ማናጀር ሁ ዊሚንግ ፕሮጀክቱን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። አሁን ላይ የኤሌክትሪክ ምሰሶዎችን የማቆም ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፤ በቀጣይ የማገናኘት እና የሙከራ ስራ መሆኑን ጠቁመዋል።   በፕሮጀክቱ የሎት አንድ ሳይት መሀንዲስ አረአያ ጌታሁን በምስራቅ ሪጅን ካሉ ሳይቶች ውስጥ ሶስቱ መጠናቀቃቸውን ገልጸው፤ በተያዘለት ጊዜ ማጠናቀቅ የሚያስችል ስራም እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።
በዞኑ ያለውን የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም ከዝናብ ጠባቂነት ለመላቀቅ በተሠራው ሥራ ውጤት ተገኝቷል
Mar 30, 2026 68
ጅማ፤ መጋቢት 21/2018(ኢዜአ)፡-በጅማ ዞን ያለውን የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም ከዝናብ ጠባቂነት በመላቀቅ በዓመት ሁለት ጊዜ ለማምረት በተሠራው ሥራ አበረታች ውጤት እየተገኘ ነው። በዞኑ ከ930 በላይ የውኃ ምንጮች ያሉ ሲሆን፣ ይህን የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም አርሶ አደሩ በመስኖ የተሻለ ምርት እንዲያመርት ሲሠራ ቆይቷል። የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም እንዳሉት፤ በዘንድሮ ዓመት 63 ሺህ 180 ሄክታር መሬት በአትክልት ምርት ተሸፍኗል።   ከዚህም 10 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል የአትክልት ምርት ተሰብስቧል ነው ያሉት። ከዚህ ቀደም በቂ የገበያ ትስስር ባለመፈጠሩ አርሶ አደሩ ምርቱን ለገበያ ለማቅረብ ሲቸገር መቆየቱን የተናገሩት ኃላፊው፤ አሁን ላይ ይህ ችግር ተቀርፎ ነጋዴው ያለማንም ጣልቃ ገብነት በቀጥታ ወደ ስፍራው ሄዶ ከአርሶ አደሩ እንዲረከብ እየተደረገ ነው ብለዋል። በሂደቱ አርሶ አደሮች ተደራድረው የራሳቸውን የዋጋ ተመን በማውጣት ምርታቸውን በስምምነት እንዲያቀርቡ መንገድ መክፈቱን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪም ሴት አርሶ አደሮችን በማደራጀት አምርተው ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። በጅማ ዞን ሰኮሩ ወረዳ ኡንኩሬ ቀበሌ ነዋሪ የሆነችው ሰብለ አየለ፤ በሽንኩርት፣ ቲማቲም፣ ጥቅል ጎመን እና በሌሎችም የአትክልት ምርቶች ተሰማርታ ውጤታማ መሆኗን ትናገራለች። የስራውን ውጤታማነት በመረዳት ስድስት ሴቶችን ጨምራ በማደራጀት በዚህ ዓመት ከ350 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘቷን ገልፃ በቀጣይም እየተሰበሰበ ካለው የሽንኩርት ምርት የ300 ሺህ ብር ገቢ ለማግኘት ማቀዷን ነው የገለጸችው። በአካባቢው ያለውን ውኃ በመጠቀም ወደፊት በስፋት አምርታ ለበርካቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ማቀዷንም አክላለች። ሌላኛው የጅማ ዞን ቀርሳ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ነጂብ አባ ራያ የውሀ ፓምፕ በመጠቀም አምርተው ለገበያ በማቅረብ ከ 300 ሺህ ብር በላይ ገቢ አግኝተዋል። በቀጣይም የተሻለ ምርት በማምረት ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እየሰሩ ሲሆን አሁን ላይም ተጨማሪ የሽንኩርት ምርት ለገበያ እያቀረብኩ ነው ብለዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በሚቀጥለው ክረምት የሚተከል የቡና ችግኝ ተዘጋጀ
Mar 30, 2026 59
አምቦ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በ220 የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች በሚቀጥለው ክረምት የሚተከል የቡና ችግኝ መዘጋጀቱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ የቡና፣ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ቡድን መሪ አቶ ቶሎሳ አራርሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ አርሶ አደሩን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በቡናና ፍራፍሬ ልማት በማሳተፍ ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ እየተሠራ ይገኛል። ለዚህም በመጪው ክረምት 5 ነጥብ 7 ሚሊዮን የቡና ችግኝ ለማዘጋጀት ታቅዶ፣ እስካሁን 5 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞች ተዘጋጅተዋል። እንደ ቡድን መሪው ገለጻ፤ ችግኞቹ ከጅማ ግብርና ምርምር ማዕከል የተገኙ የተሻሻሉ ዝርያዎች ሲሆኑ፣ በሽታን የመቋቋም አቅም ያላቸውና በሦስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ምርት መስጠት የሚጀምሩ ናቸው። የችግኝ ዝግጅቱ በ220 የመንግሥትና የግል የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እየተከናወነ ሲሆን፣ በሥራው ላይ 16 ሺህ 415 አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን ገልጸዋል። የተዘጋጀው የቡና ችግኝ ሲተከል አንድ ሺህ ሄክታር ገደማ አዲስ መሬት በቡና መሸፈን እንደሚያስችልም ጠቅሰዋል። ከአዲስ ተከላው በተጓዳኝ ያረጁና ከምርት ውጭ የሆኑ የቡና ዛፎችን የማደስ ሥራም እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።
የአመራር አባላት ኢንተርፕርነርሽፕ ክህሎት መጎልበት ለፈጠራና ለለውጥ መሠረት ነው- ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ
Mar 30, 2026 154
አዲስ አበባ፤መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦የአመራር አባላቱ ኢንተርፕርነርሽፕ ክህሎት መጎልበት ለፈጠራና ለለውጥ መሠረት ነው ሲሉ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኢንተርፕረነርሽፕ ልማት ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት "አመራርና የመጪው ዘመን ዝግጁነት "በሚል መሪ ሀሳብ የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና መስጠት ጀምሯል።   ሥልጠናው የአመራር አባላት ሥራቸውን በአንተርፕረነርሽፕ አስተሳሰብ እንዲመሩና ለተለዋዋጭ የሥራ አካባቢዎች ዝግጁ እንዲሆኑ ታስቦ የተዘጋጀ እንደሆነ ተመላክቷል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ በዚሁ ወቅት ሥልጠናው የምክር ቤት አባላት ካላችሁ የላቀ የሕዝብ አመራር ልምድ በመነሳት ሀገራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎችን በላቀ ብስለትና በሥራ ፈጠራነት መንፈስ እንድትቀርጹ ለማገዝ ነው ብለዋል። አባላቱ ያላቸው ዕውቀትና ልምድ ውጤታማ እና ፍሬያማ የሆኑ ሥራዎች ለመስራት የሚያግዝ እንደሆነ ጠቁመዋል። ይህም ችግሮችን በፈጠራ፣ በፍጥነት እንዲሁም በባለቤትነት መንፈስ ለመፍታትና አዳዲስ የአገልግሎት ዘርፎችን ለመፍጠር የሚያስችል ነው ብለዋል።   የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በበኩላቸው፤ የዘመኑን ፈጣን ለውጥ ለመቋቋም የአመራሩ የሥራ መርህ መዘመን እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል። የአመራር አባላት እንደ አንድ ሥራ ፈጣሪ የችግሮችን መፍትሔ በአዲስ የፈጠራ መንገድ የመቅረጽ፣አዳዲስ ዕድሎችን የመለየት እና በሥራ ሂደት ውስጥ የመፍጠንና የመፍጠር ብቃት ሊኖራቸው እንደሚገባም ገልጸዋል። በመሆኑም ይህ ሥልጠና በምክር ቤቱ አባላት ዘንድ የስትራቴጂክ አመራር ክህሎትን ከማሳደጉ ባሻገር ሀገራዊ የልማት ግቦችን በብቃት ለማሳካት የሚረዳ የተቀናጀ የአሠራር ሥርዓት ለመገንባት ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፣ የምክር ቤቱ አባላትና የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
ባለፉት ዓመታት በሁሉም ዘርፎች የተመዘገቡ መጠነ-ሰፊ ስኬቶች የኢትዮጵያ መጪው ጊዜ ብሩህ ለመሆኑ አመላካቾች ናቸው
Mar 30, 2026 148
አዲስ አበባ፤መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦ባለፉት ዓመታት በሁሉም ዘርፎች የተመዘገቡ መጠነ-ሰፊ ስኬቶች የኢትዮጵያ መጪው ጊዜ ብሩህ ለመሆኑ አመላካቾች ናቸው ሲሉ የብልፅግና ፓርቲ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልና የኢኮኖሚ ብልፅግና ክላስተር ሰብሳቢ አቶ መላኩ አለበል ገለጹ። በብልፅግና ፓርቲ የኢኮኖሚ ብልፅግና ክላስተር የሴቶችና ወጣቶች የንቅናቄ መድረክ እየተካሄደ ነው።   የብልፅግና ፓርቲ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባልና የኢኮኖሚ ብልፅግና ክላስተር ሰብሳቢ አቶ መላኩ አለበል በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የመድረኩ ዋነኛ ዓላማ አባላት ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርጉና የሚጠበቅባቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ማስቻል ነው። ምርጫው ነፃ፣ተዓማኒ፣ሰላማዊ እና ፍትሐዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የሴቶችና የወጣቶች ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመው፤ይህም ቅቡልነት ያለው መንግሥት ለመገንባት ዓይነተኛ ሚና እንዳለው ተናግረዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት የሴቶችንና የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አመርቂ ስራዎች መከናወናቸውን አብራርተዋል።   ለአብነትም ሴቶች በፓርቲው ውስጥ ንቁ ተሳታፊ እንዲሆኑ፣ ወደ አመራርነት እንዲመጡ እና በከተማም ሆነ በገጠር የኢኮኖሚ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስታውቀዋል። በሌላ መልኩ የወጣቶች የፖለቲካና የአመራርነት ድርሻ እንዲያድግ ከመደረጉም በላይ፣በስራ ዕድል ፈጠራ እና በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄና በሌሎችም ዘርፎች ያላቸው ተሳትፎ እንዲጎለብት ተደርጓል ብለዋል። ብልፅግና ፓርቲ ባለፉት አምስት ዓመታት ለህዝቡ የገባውን ቃል ሙሉ በሙሉ ማሳካቱ ለቀጣዩ ምርጫ ትልቅ ስንቅ እንደሚሆን ጠቁመዋል። ባለፉት ዓመታት በኢኮኖሚ፣ በፖለቲካ እና በሌሎችም ዘርፎች የተገኙ ውጤቶች መጪው ጊዜ ብሩህ ለመሆኑ አመላካቾች ናቸው ብለዋል።   የብልፅግና ፓርቲ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልና የክላስተሩ የፖለቲካ ዘርፍ ሰብሳቢ ጫልቱ ሳኒ በበኩላቸው፤ፓርቲው መሰረታዊ የዜጎችን ጥያቄ ከመመለስ አኳያ ውጤታማ ስራዎችን ማከናወኑን ገልጸዋል። የዴሞክራሲ ጥያቄን ለመመለስ የሚያስችሉ ተቋማት መገንባታቸውንና እውነተኛ የዲሞክራሲ ስርዓት ለመገንባት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል። ባለፉት ዓመታት ሀገራዊ አንድነትን ከፍ የሚያደርጉ ስራዎች ተሰርተዋል፤ይህም የዳር ተመልካችነት ቀርቶ ሁሉም ዜጋ በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እኩል ተሳታፊ እንዲሆን አስችሏል ብለዋል። 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለሁሉም እኩል ሜዳ የሚረጋገጥበት መሆኑን ጠቅሰው፣ ምርጫው ቅቡልነት ያለው የሀገረ መንግስት ግንባታን እውን ለማድረግ እንደሚረዳ አስገንዝበዋል። ሂደቱንም ሆነ የግቡ ስኬታማነት ለማረጋገጥ በከፍተኛ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት በኢኮኖሚና በፖለቲካው ዘርፍ የተገኙ ውጤቶች መጪው ጊዜ ለብልፅግና ብሩህ እንዲሆን የሚያደርጉ መሆናቸውን ጠቁመዋል።  
የተሰማራንበት የፍራፍሬና አትክልት ልማት ተጠቃሚ አድርጎናል-አርሶ አደሮች
Mar 30, 2026 72
ሀላባ ቁሊቶ፤መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦በፍራፍሬና አትክልት ልማት በመሰማራታቸው ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው ማደጉን በሀላባ ዞን የዌራ ዲጆ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ። የዌራ ዲጆ ወረዳ ከዚህ ቀደም በጎርፍ አደጋና በመሬት ተዳፋትነት ምክንያት ለልማት አስቸጋሪ የነበረ ቢሆንም፣በአሁኑ ወቅት ግን በተከታታይ የአካባቢ ጥበቃ ስራ በመሰራቱ መሬቱ የተሻለ ምርት እየሰጠ መሆኑም ተገልጿል። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የወረዳው አርሶ አደሮች እንደገለፁት፥ ቀደም ሲል አካባቢው ዝናብ በዘነበ ቁጥር ለጎርፍ ተጋላጭ በመሆኑ አርሶ አደሩ እርዳታ ጠባቂ ሆኖ ቆይቷል። በአካባቢው የጎርፍ መቀልበሻ ግንባታ በመከናወኑ እና በሶላር ሃይል የሚሰራ የከርሰ ምድር ውሃ ጥቅም ላይ እንዲውል በመደረጉ፣ አካባቢው ዛሬ ላይ የሌሎች ተሞክሮ መቅሰሚያ ማዕከል ለመሆን በቅቷል ብለዋል። በኩታ ገጠም በመደራጀት አትክልትና ፍራፍሬ በማልማት ላይ የሚገኙ አርሶ አደሮች "ቀደም ሲል በሴፍቲኔት እርዳታ እንኖር ነበር፤ አሁን ግን በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ምርታችንን ለገበያ በማቅረብ ህይወታችንን እየለወጥን ነው" ብለዋል። ሌላው የመንገሳ ኢንተርፕራይዝ አባል ዱባለ ሁሴን፤ አምስት ሆነው በተደራጁ በስድስት ወራት ውስጥ በ4 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ የጓሮ አትክልቶችን በማልማት ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ገልጿል። በአካባቢው በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት የተሰማራ የእርሻ ድርጅት ስራ አስኪያጅ አደም ኑርአብደላ፤ በ30 ሄክታር መሬት ላይ በመስኖ ልማት እየሰሩ መሆኑን ገልጸው፣ ከዚህ ውስጥ በ4 ሄክታር ላይ አቮካዶና ሙዝ በማልማት ውጤት ማግኘት መጀመራቸውን ተናግረዋል። ልማቱ ለአካባቢው ነዋሪዎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ ምርትን በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረበ ይገኛል። የሀላባ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ ሀጂ ኑሪዬ እንደገለጹት፥ ወረዳውን ከእርዳታ ጠባቂነት ለማውጣት ሰፊ ስራ ተሰርቷል። "በ13 ቀበሌዎች ይከሰት የነበረውን ጎርፍ ለመከላከል ከ6 ኪሎ ሜትር በላይ የጎርፍ መቀልበሻ ተገንብቷል ብለዋል። በተጨማሪም ከ86 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ የከርሰ ምድር ውሃን በሶላር ሃይል ለመስኖ እንዲውል ተደርጓል" ነው ያሉት። ይህም አርሶ አደሩ ከችግር ወጥቶ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን አመልክተዋል።
የአፋር ክልል የመስኖ ተፋሰስ ለዝናብ አጠር አካባቢዎች ትልቅ የመማሪያ ሰነድ ነው-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Mar 30, 2026 148
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ)፦የአፋር ክልል የመስኖ ተፋሰስ ስራ ከዓመት እስከ ዝናብ አጠር ለሆኑ አካባቢዎች ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፥በአዋሽ ወንዝ ተፋሰስ በመሥኖ እየለማ ያለው የሱፍ ምርት ለተሻገረ ግብርና እና ለተሻገረ ገጠር ራዕያችን ተደማሪ ሃብት ነው ብለዋል።   በክልሉ ዱብቲ ወረዳ የለማው የሱፍ ምርትም እንደቢጫው አበባ ተስፋን የሚያላብስ፤ እንደተሰበሰበው ምርት የተጨባጭ ብልጽግና አብነት መሆኑን ገልጸዋል። በአፋር ክልል ያየነው በመሥኖ ተፋሰስ በረሃ የመሰለውን ምድር የምርት መትረፍረፊያ የማድረግ ትጋት ለሌሎችም በተለይም ከዓመት እስከ ዓመት ዝናብ አጠር አካባቢዎች ትልቅ የመማሪያ ሰነድ እንደሆነም ተናግረዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ልማትን የሚያበረታታ የኢኮኖሚ ሪፎርም ማድረጓ ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ አድርጓታል
Mar 29, 2026 341
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ የአረንጓዴና የታዳሽ ኃይል ልማትን የሚያበረታታ የተሟላ የኢኮኖሚ ሪፎርም ማድረጓ በቀጣናው ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ እንዳደረጋት ተገለጸ። በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግሥታት የልማት ፕሮግራም የፖሊሲ ጥናት ማዕከል ኃላፊና በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ አማካሪ አሊ ዛፋር፤ የሀገሪቱ የኃይል አቅርቦት ምንጭ የሆነው ታዳሽ ኃይል መሆኑን ገልጸዋል።   በተለይም ከውኃ ሀብት የሚመነጨው ኃይል የኢንዱስትሪ ልማትን በማሳለጥ ሀገራዊ የልማት ግቦችን በማሳካት ኢትዮጵያን ከቀጣናው ሀገራት ጋር በኃይል ያስተሳስራል ሲሉም ለኢዜአ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ባደረገችው ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ ሪፎርም በርካታ ለውጦች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም የዋጋ ግሽበት መቀነሱንና የውጭ ምንዛሬ ክምችት መሻሻሉን አንስተዋል።   በቀጣናው ዝቅተኛ የኃይል አቅርቦት ዋጋ ያላት፣ ለኢንቨስትመንት ምቹ እና መንግሥት ለዘርፉ ከፍተኛ ድጋፍ የሚያደርግ መሆኑ ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳራሻ እንዳደረጋትም አመላክተዋል። ሀገሪቱ ያላትን የኢንቨስትመንት ዕድሎች ለማስተዋወቅ የምታደርገውን ጥረት በመጥቀስ፤ መንግሥት በታዳሽ ኃይል የሚመራ አረንጓዴ ልማትን ለማረጋገጥ ያለውን ጽኑ አቋም አድንቀዋል፡፡   ኢትዮጵያ ለአረንጓዴ ልማት ትልቅ ትኩረት በመስጠት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች እንዲበረታቱ እያደረገች መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ በአካባቢ ጥበቃና በታዳሽ ኃይል ልማት ግንባር ቀደም መሆኗን ጠቅሰው፤ ሌሎች ሀገራት ሊማሩበት የሚገባ መሆኑን በአጽንኦት ገልጸዋል፡፡
የኢንዱስትሪው ዘርፍ ለውጭ ምንዛሬ ግኝትና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ሚናውን እየተወጣ ነው
Mar 29, 2026 206
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዘአ)፡- የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ዘርፍ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን በማሳደግና ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያበረከተ መሆኑን የተለያዩ አምራቾች ገለጹ፡፡ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች በአዲስ አበባና በሸገር ከተሞች የሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ጎብኝተዋል። በዚሁ ወቅት የጎበዝ የፀሐይ ኃይል ሶላር ሴል ማምረቻ ሥራ አስኪያጅ በረከት ኃይሉ፤ ምርታቸውን በዋናነት ለአሜሪካ ገበያ እንዲሁም ወደ ካናዳ፣ ቬትናም እና መካከለኛው ምሥራቅ ሀገራት እየላኩ መሆኑን ተናግረዋል።   ድርጅቱ ለ300 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸው፤ በመንግሥት እየተደረገ ያለው ድጋፍ የማምረት ዐቅማቸውን እንዳሳደገው ለኢዜአ ገልጸዋል። የዳቺ ማኑፋክቸሪንግ ቺፍ ኮሜርሻል ኦፊሰር ቢንያም ዮሐንስ በበኩላቸው ድርጅቱ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ወደ ምርት መግባቱን አውስተው፤ በአራት ፋብሪካዎች 46 ዓይነት የታሸጉ ምግቦችን እያመረተ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እያቀረበ መሆኑን ገልጸዋል።   ይህም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ከመደገፍ ባለፈ፣ በውጭ ምንዛሬ ግኝት ረገድ የበኩሉን አስተዋጽዖ እያበረከተ መሆኑን ነው ያስገነዘቡት። መንግሥት እያደረገ ያለው ድጋፍና ክትትልም የድርጅቱን የማምረት ዐቅም እንዳሳደገው አረጋግጠዋል። ድርጅታቸው የተለያዩ የስፖርት ትጥቆችንና አልባሳትን እያመረተ እንደሚገኝ የገለጹት ደግሞ የሀብቴ ጋርመንት ምክትል ሥራ አስፈፃሚ ሐይማኖት ሙሉጌታ ናቸው።   ከሀገር ውስጥ አቅርቦት ባለፈ፤ ምርቶቻቸውን ጋና፣ ላይቤሪያ እና ቡሩንዲን ጨምሮ ወደ ተለያዩ ሀገራት እየላኩ መሆናቸውን አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅት ድርጅቱ 400 ሠራተኞች ያሉት ሲሆን፤ በሚቀጥሉት ስድስት ወራት የሠራተኞችን ቁጥር በ50 በመቶ ለማሳደግ እየሠራ መሆኑንም አስታውቀዋል። የካይት ማኑፋክቸሪንግ የግዢና ሽያጭ ኃላፊ አሸናፊ ፀጋ በበኩላቸው፤ ድርጅቱ የተለያዩ የምርት ማሸጊያዎችን በማምረት ለተለያዩ ኢንዱስትሪዎች እያቀረበ ነው ብለዋል።   እስካሁን ለ220 ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉንም ጠቁመዋል። መንግሥት የመሬትና የፋይናንስ አቅርቦትን ጨምሮ እያደረገ ያለው ድጋፍ ድርጅቱ የማምረት ዐቅሙን እንዲያሳድግ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያደረገ መሆኑንም አመላክተዋል።
የአፋር ሕዝብ በረሃውን በማለምለምና የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ጥንካሬ በመገንባት አለኝታነቱን ዳግም እያደሰ ይገኛል
Mar 28, 2026 423
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ የአፋር ሕዝብ በረሃውን በማለምለምና የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ጥንካሬ በመገንባት አለኝታነቱን ዳግም እያደሰ ይገኛል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የተንዳሆ መስኖ ልማት የማጠናቀቂያ እና መልሶ ግንባታ ፕሮጀክት ዛሬ መርቀዋል።   የአፋር ሕዝብ በረሃውን በማለምለምና የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ጥንካሬ በመገንባት አለኝታነቱን ዳግም እያደሰ ይገኛል ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው ለእኛ ሉዓላዊነት ማለት ዳር ድንበርን ከመጠበቅ ባሻገር፣ የዜጎችን አንገት የሚያስደፋውን የልመና እጅ ሰብሮ በራስ ምርት መቆም ነው ብለዋል። የአፋር ሕዝብ ለዘመናት የኢትዮጵያን ዳር ድንበር በንቃትና በጀግንነት ሲጠብቅ የኖረ የቁርጥ ቀን የሀገር ባለውለታ መሆኑንም አውስተዋል። ለምርቃት የበቃው የተንዳሆ መስኖ ልማት የማጠናቀቂያ እና መልሶ ግንባታ ፕሮጀክት፣ የምግብ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥ ትግላችን የድል ዓርማ ነው ብለዋል። ለዓመታት ተጓትቶ፣ ተስፋ አስቆርጦና የጎርፍ ሥጋት ሆኖ የቆየውን ግድብ፣ በቆራጥ አመራርና በፈጣን አፈጻጸም ወደ ልማት አውታር መቀየሩን ተናግረዋል። ይህ ፕሮጀክት ለምድራችን በረከት፣ ለሕዝባችን የብልጽግና ምንጭ እንዲሆን ዳግም ተወልዷል ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ። እውነተኛ ነጻነትና ምሉዕ ክብር የሚረጋገጠው በራስ ማሳ ላይ በሚለማ ሰብል፣ በራስ ጉልበት በሚገራ ውኃና ከማንም እጅ በማይጠበቅ የዜጎች የዕለት ጉርስ መሆኑንም አመልክተዋል።   የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተነሣነውም የዜጋን ክብርና የሀገርን የህልውና መሠረት ለማጽናት ነው የዚህ ዋናዎቹ ዐቅሞቻችን ደግሞ ያልተነካው የበረሃ ለም አፈራችን፣ ውኃችን፣ ትጉህ ሕዝባችንና የመስኖ አውታሮቻችን ናቸው ብለዋል። ለእኛ መስኖ ማለት የዝናብ ጠባቂነትን ታሪክ መዝጋት ነው፤ መስኖ ተለዋዋጭ የሆነውን የዓለም ጂኦ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ውጥረት የምንቋቋምበት ብቸኛውና አስተማማኙ መከታችን ነው ሲሉም ገልጸዋል። የቆላማ አካባቢዎቻችንን እምቅ ሀብት ማልማትና የዜጎቻችንን ሕይወት በዘመናዊ የኮሪደር ልማት ማሣለጥ የወደፊት ዕጣ ፈንታችንን የመወሰን ጉዳይ እንደሆነም ነው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያነሱት። ቃልን በተግባር፣ ሐሳብን በውጤት እየለወጥን፣ አርሶ አደሩን፣ አርብቶ አደሩንና ባለ ሀብቱን ያስተሣሠረ የልማት ሠንሰለት በመፍጠር፣ ኢትዮጵያን በምግብ ራሷን የቻለች ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም የምትተርፍ የብልጽግና ተምሳሌት እናደርጋታለን ብለዋል።
የፌዴራል መንግሥት ተንዳሆን ከችግር አውጥቶ ወደ ልማት አውታር መልሶታል - ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ
Mar 28, 2026 356
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ የፌዴራል መንግሥት ተንዳሆን ከችግርና ስጋት አውጥቶ የአፋርን ክልል ተጠቃሚ ወደሚያደርግ የልማት አውታር መልሶታል ሲሉ የአፋር ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በአፋር ክልል የተንዳሆ መስኖ መሠረተ ልማት ማጠናቀቂያና መልሶ ግንባታ ፕሮጀክትን መርቀው አገልግሎት አስጀምረዋል።   የአፋር ክልል ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ የተንዳሆ የመስኖ ፕሮጀክት ዱብቲ፣ የሠመራ ሎጊያ ክፍለ ከተሞችን ጨምሮ ስድስት ወረዳዎችን በቀጥታ ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል። የአፋር ሕዝብ በአዋሽ ወንዝ ጎርፍና በድርቅ በውሃ እጥረት ጉዳት ሲደርስበት መቆየቱን አንስተው፤ አሁን ግን ችግሩ እየተቀረፈ ነው ብለዋል። የተንዳሆ ግድብ ውሃ ሲሞላ የማስተንፈሻ ቦዩ የመቆጣጠሪያ ሥርዓቱ የተስተካከለ ስላልነበር ማህበረሰቡ ላይ ትልቅ የጎርፍ ስጋት ሆኖ እንደነበር አስታውሰዋል። በመሆኑም የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር አፋርን ከጎርፍ አደጋ እየታደገና የውሃ አቅምን በመጠቀም የውሃ እጥረትን እየፈታ መሆኑን ተናግረዋል።   ለፌደራል መንግሥቱ ትልቅ አድናቆት አለኝ ያሉት ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ፤ በቢሊየን ሀብት አውጥቶ ተንዳሆን ወደዚህ ደረጃ ማድረሱ ቀላል አይደለም ነው ያሉት። በአፋር ክልል በርካታ የቆላማ ልማትና የመስኖ ግድቦች እየተገነቡ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለዚህም የፌዴራል መንግሥቱን አመሥግነዋል።
የተንዳሆ መስኖ መሠረተ ልማት እስከ 60 ሺህ ሄክታር መሬት የማልማት አቅም አለው
Mar 28, 2026 291
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ የተንዳሆ መስኖ መሠረተ ልማት እስከ 60 ሺህ ሄክታር መሬት የማልማት አቅም እንዳለው የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ(ዶ/ር) ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የተንዳሆ መስኖ ልማት ማጠናቀቂያና መልሶ ግንባታ ፕሮጀክትን መርቀዋል።   በዚሁ ወቅት የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ(ዶ/ር)፤ ባለፉት ጥቂት ወራት በጠንካራ የፕሮጀክት አመራር አምስት የመስኖ ፕሮጀክቶች ተጠናቅቀው ወደ አገልግሎት መግባታቸውን አንስተዋል። ይህም በፌዴራል መንግሥት ያላሰለሰ ድጋፍና በክልሎች ቁርጠኝነት የተሳካ ነው ብለዋል።   የተንዳሆ ፕሮጀክት ስኬትም የግብርና ምርታማነት የተስፋ ምንጭና የኢኮኖሚ መሠረት መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ በመጠናቀቁ የአካባቢው አርሶና አርብቶ አደሮች ከዝናብ ጥገኝነት ተላቀው በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ በማምረት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለተጀመረው ጥረት ላቅ ያለ ድርሻ እንዳለው ተናግረዋል። ፕሮጀክቱ ከ15 ዓመታት በፊት ቢጀመርም የማህበረሰቡ የስጋት ምንጭ ከመሆን ያለፈ ጥቅም ሳይሰጥ መቆየቱን ተናግረዋል። የውሃ ፍሰቱን መቆጣጠር የሚያስችል ሥርዓት በአግባቡ ስላልተዘረጋለት ተጨማሪ ችግር እንደነበረበትም ጠቅሰዋል። አሁን ላይም የፕሮጀክቱን ውስብስብ ችግሮች እንዲቃለሉ በማድረግ ወደ ሥራ መግባቱን አንስተዋል። ባለፉት ጥቂት ዓመታት የግድቡን ሁኔታ በማጥናት የውሃ ማስተንፈሻ ችግሮች እንዲስተካከሉ መደረጉንና 40 ኪሎ ሜትር የካናል ዕድሳት ሥራ መሰራቱን ገልጸዋል። ማህበረሰቡንና ካናሎቹን ከጎርፍ ለመከላከልም 27 ኪሎ ሜትር የድጋፍ ግንብ መገንባቱን አስታውቀዋል። የተንዳሆ የመስኖ መሠረተ ልማት 60 ሺህ ሄክታር የማልማት አቅም እንዳለው ጠቅሰው፤ በአሁኑ ወቅት 33 ሺህ ሄክታር ለማልማት ዝግጁ ሆኗል ብለዋል። ከዚህ ውስጥም 23 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ የመስኖ ልማቶች መሸፈኑንም ሚኒስትሩ አስረድተዋል።
የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የመደመር መንግሥት አንዱና ዋናው ተልዕኮ ነው
Mar 28, 2026 208
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የመደመር መንግሥት አንዱና ዋናው ተልዕኮ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን፤ ይህንን ያሉት በአፋር ክልል የሚገኘውን የተንዳሆ መስኖ ልማት የማጠናቀቂያ እና የመልሶ ግንባታ ፕሮጀክት መርቀው ለአገልግሎት በከፈቱበት ወቅት ነው።   የምግብ ሉዓላዊነት ዜጎች በራሳቸው ሀብት፣ ዕውቀትና ጉልበት እንዲሁም እንደ አካባቢው ሥነ-ምኅዳር አመቺነት የተለያዩ ሰብሎችን በማምረት፣ የሥነ-ምግብ ባህላቸው ተጠብቆ እንዲመገቡ ማስቻል መሆኑን አብራርተዋል። ይህም ኢትዮጵያ በተለይ በስንዴ ልማት ስኬት ማስመዝገቧና ከውጭ የሚገባውን ምርት ማስቆም መቻሉን፣ እንደ ኮቪድ-19 ያሉ ዓለም አቀፍ ቀውሶችን በድል እንድትወጣ ማድረጉንም አንስተዋል። መንግሥት ግብርናን ለማዘመንና ምርታማነትን ለማሳደግ ለመስኖ ልማት ልዩ ትኩረት መስጠቱን የገለጹት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለዚህም ይረዳ ዘንድ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ራሱን ችሎ እንዲቋቋም መደረጉን አስታውሰዋል። ዘርፉ የበጀትና የፋይናንስ ነጻነት እንዲኖረው በማድረግም፣ መንግሥት በየዓመቱ ለመስኖ መሠረተ ልማት ግንባታ ከ20 ቢሊየን ብር በላይ በጀት እየመደበ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በዚህ ምክንያት ላለፉት 20 ዓመታትና ከዚያ በላይ በፕሮጀክት አፈጻጸም ውስንነት ተጓትተው የቆዩ እንደ መገጭና አርጆ ያሉ ፕሮጀክቶች በፍጥነት እየተጠናቀቁ መሆኑን ገልጸዋል። በተጨማሪም የጎዴ፣ የወልመል፣ የቄጦ፣ የጊዳቦ፣ የታችኛው ርብ እና ከሰም የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቅቀው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸው የመንግሥትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል።   ዛሬ የተመረቀውን የተንዳሆ መስኖ ግድብ ፕሮጀክት ከ15 ዓመታት በፊት ቢገነባም መሠረታዊ የሆኑ የማጠናቀቂያ ሥራዎች ባለመከናወኑ ለጎርፍ ሥጋት ሆኖ መቆየቱን አስታውሰዋል። አሁን ላይ በተደረገለት ከፍተኛ ጥገናና የማጠናቀቂያ ሥራ ወደ አገልግሎት መመለሱ ትልቅ ስኬት መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገልጸዋል። መንግሥት መስኖን የኢኮኖሚ ዋነኛ ምሰሶ በማድረጉ የሀገሪቱን የመስኖ ሽፋን ከለውጡ በፊት ከነበረበት 490ሺህ ሄክታር ወደ ሁለት ነጥብ አራት ሚሊየን ሄክታር ከፍ ማለቱን አንስተዋል። በመስኖ ሊለማ የሚችል 10 ሚሊየን ሄክታር መሬት መኖሩን ጠቅሰው፤ ከዚህም አብዛኛው የሚገኘው እንደ አፋር ክልል ባሉ ቆላማ አካባቢዎች ነው ብለዋል።   የአፋር ክልል ሚሊዮኖችን መመገብ የሚችሉ ዕምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችና ተፋሰሶች ባለቤት መሆኑን ጠቁመው፤ ክልሎች ከተገነቡ የመስኖ መሠረተ ልማቶች ጋር ተናብበው በመሥራት አርሶና አርብቶ አደሮች፣ ወጣቶች፣ ሴቶችና ባለሀብቶች በስፋት የሚሳተፉበትን ምቹ ሁኔታ እንዲፈጥሩም ጥሪ አቅርበዋል።
በክልሉ የገቢ አቅምን በማሳደግ ልማትና እድገት የማፋጠን ስራ ይጠናከራል - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Mar 28, 2026 117
ሀዋሳ ፤መጋቢት 19/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የገቢ አቅምን በማሳደግ ልማትና እድገት የማፋጠን ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። በክልሉ የሞዴል ግብር ከፋዮች የእውቅናና የሽልማት መርሃ ግብር በሀዋሳ ከተማ ተካሂዷል። ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በመርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ ክልሉ ሲመሰረት የነበረው የ4 ቢሊዮን ብር የገቢ አቅም በአሁኑ ወቅት ከ40 በመቶ በላይ እድገት አሳይቷል።   የገቢ አሰባሰብ ሂደቱን በማዘመንና ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ለህዝቡ የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በዚህ ሂደትም የታማኝ ግብር ከፋዮች ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰው፤ "ግብር ከፋዮች የሀገር ባለውለታ በመሆናቸው ክብር ይገባቸዋል" ብለዋል።   በሀዋሳ ከተማ የታየው ፈጣን የመሰረተ ልማት ለውጥ የታማኝ ግብር ከፋዮች ውጤት መሆኑን የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ በሌሎች የክልሉ አካባቢዎች ያለውን የኢኮኖሚ አቅም በአግባቡ ለመጠቀም አመራሩ ተግቶ መስራት እንዳለበት አሳስበዋል።   የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ደምሴ እሳቱ በበኩላቸው፤ በ2017 የግብር ዘመን 14 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን ገልጸው፤ ይህም ከቀደመው ዓመት የ4 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል። በተያዘው የ2018 በጀት ዓመት ስምንት ወራት ውስጥም 14 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ የእቅዱን 94 በመቶ ማሳካት ተችሏል ብለዋል። ለዚህ ስኬት በቴክኖሎጂ የተደገፈ የገቢ አሰባሰብ ስርዓት መዘርጋቱና የሞዴል ግብር ከፋዮች ታማኝነት ትልቅ ሚና ማበርከቱን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።   በ2017 የግብር ዘመን ከ57 ሚሊዮን ብር በላይ በመክፈል ግንባር ቀደም የሆኑት የኢታብ ሳሙና ፋብሪካ ባለቤትና ማኔጂንግ ዳይሬክተር መምህር ተስፋዬ አበበ፤ ግብርን በታማኝነት መክፈል ሀገራዊ ግዴታና የድርጅቱ ባህል መሆኑን ተናግረዋል። የዘላለም ኮንስትራክሽን ባለቤት ኢንጂነር ዘላለም ወልደአማኑኤል በበኩላቸው፤ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱ በመክፈላቸው እውቅና እንደተሰጣቸው ገልጸው፤ መንግስት የሚሰበስበው ገቢ በከተሞች የመሰረተ ልማትና በኮሪደር ልማት ስራዎች ላይ እያመጣ ያለውን ለውጥ በምሳሌነት ጠቅሰዋል።   በዕለቱ እውቅናና ሽልማት የተሰጣቸው 77 የደረጃ "ሀ" እና "ለ" ግብር ከፋዮች፣ የልማት ድርጅቶችና የህብረት ስራ ማህበራት ሲሆኑ፤ እነዚህ አካላት ከ700 ሺህ እስከ 57 ሚሊዮን ብር ግብር የከፈሉ መሆናቸው ታውቋል።  
በሸገር ከተማ ዘመናዊ የከተማ አስተዳደር ስርዓትን በመተግበር የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ ትኩረት ተሰጥቷል
Mar 28, 2026 84
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ ዘመናዊ የከተማ አስተዳደር ስርዓትን በመተግበር የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የሸገር ከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ(ዶ/ር) ገለጹ። በከተማው የአርሶ አደሮች መሠረታዊ የኑሮ ማሻሻያ ሁኔታ ላይ ያተኮረ ወርክሾፕ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ተካሂዷል።   ከንቲባ ተሾመ አዱኛ(ዶ/ር) በመድረኩ እንደገለጹት፤ ባለፉት ሦስት ዓመታት ጥናትን መሠረት በማድረግ የሸገር ከተማን ለማሳደግና ለማዘመን የተለያዩ ተግባራት ሲከናወኑ ቆይተዋል። በቴክኖሎጂ የታገዙ ተግባራትን በማከናወን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገትን ለማስመዝገብ ትኩረት እንደተሰጠው ጠቁመው፤ ከተማው ከተመሰረተ ጀምሮ ዘመናዊ ፕላንን ጨምሮ ከተማዋን የማዘመን ስራዎች ስኬታማ እየሆኑ መምጣታቸውን አብራርተዋል። በተለይም የከተማውን አርሶ አደር የአኗኗር ዘይቤ በማሻሸል በኩል ወርክሾፑ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህም በእቅድና በአፈፃፀም መካከል ያለውን ክፍተት ለማጥበብ፣ ልማቱን በተጨባጭ መረጃ ለመመዘንና የተገኘውን ለውጥ ለማስቀጠል ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል። በአጠቃላይ ዘመናዊ የከተማ አስተዳደር ስርዓትን በመተግባር የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   የሸገር ከተማ አስተዳደር ፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ አህመድ ቶፊቅ በበኩላቸው፤ ከተማው አርሶ አደሩን ማዕከል ባደረገ አዲስ እሳቤ የተመሰረተ መሆኑን ተናግረዋል። የአርሶ አደሩን ሕይወት ለመለወጥና ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ ጥናቶች እየተከናወኑ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ከተማውንና አርሶ አደሩን በማቀራረብ የነበረውን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስተጋብር ስብራት ለመጠገን እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ አርሶ አደሮችን ከእርሻ ስራ ወደ ኢንዱስትሪ፣ የእንስሳት እርባታ፣ ንግድና አገልግሎት ዘርፎች ለማሸጋገር በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።   በወርክሾፑ ጥናታዊ ጽሁፍ ያቀረቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የምግብ ዋስትና ዘርፍ ተመራማሪ መስከረም አቢ፤ ከተሜነት የኢኮኖሚ እድገትን በማፋጠን በኩል ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። የአርሶ አደሩን ሕይወት ለማሻሻል እንደ ትምህርትና ጤና ያሉ መሠረተ ልማቶችን ማስፋፋት፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ምርትና ምርታማነትን መጨመር እና የቁጠባ ባህልን ማሳደግ ላይ በትኩረት መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነትና የከተማዋን እድገት አመዛዝኖ ማስኬድ ለከተማዋ ዘላቂ ስኬት ወሳኝ መሆኑን ምክረ ሀሳብ አቅርበዋል።
በአፋር ክልል የአዋሽ ወንዝን በመጠቀም በመስኖ የለማው የሣር መኖ እርሻ፣ የተፈጥሮን ልግስና በአግባቡ የመጠቀማችን ማሳያ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Mar 28, 2026 129
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል የአዋሽ ወንዝን በመጠቀም በመስኖ የለማው የሣር መኖ እርሻ፣ የተፈጥሮን ልግስና በአግባቡ የመጠቀማችን ማሳያ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት በአፋር ክልል ዞን አንድ፣ አይሳይታ ወረዳ፣ የአዋሽ ወንዝን በመጠቀም የለማውን የሣር እና መኖ እርሻን ጎብኝተናል ብለዋል። በወረዳው 2 ሺህ 540 ሄክታር ላይ እየለማ የሚገኘውን የእንስሳት መኖ ሣር፣ የማምረት የማቀነባበር እና ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ የማቅረብ ሥራ እየተሠራ ነው ሲሉም ገልጸዋል።   በመስኖ ሥራው ለአካባቢው አርብቶ አደር የቴክኖሎጂ እና የተሻሻለ የዘር ሽግግር እየተደረገ ይገኛል ነው ያሉት በመልዕክታቸው። በማሳው ላይ ለእንስሳት የወተት ምርታማነት ወሳኝ የሆኑ የሣር ዓይነቶች እየተመረቱ እንደሚገኙ አይተናል ብለዋል። በመስኖ የሣር ልማት እና ማቀነባበር ለ1ሺህ ዜጎቻችን የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸዋል ሲሉም አክለዋል። ከእንስሳት ሀብት ልማት ማሳደጊያነቱ በተጨማሪ ለሌማት ትሩፋት ሀገራዊ ኢንሼቲቭ ታላቅ አስተዋጽዖ እያበረከተ ነው ብለዋል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት።   በአፋር የአዋሽ ወንዝን በመጠቀም የተሠራው የመስኖ ሥራ ለሌላውም የኢትዮጵያ አካባቢ ዝናብን ጠብቆ ከማምረት ይልቅ በየአቅጣጫው ያሉ ወንዞቻችንን መጠቀም እንደሚገባ የሚያስተምር ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም