ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
 በጥምቀት በዓል ላይ የሚታየው ስነ-ስርዓት፣ ውበትና ድምቀት አስደናቂ  ነው-  የውጭ ሀገራት ጎብኚዎች
Jan 19, 2026 53
አዲስ አበባ፤ጥር 11/2018 (ኢዜአ)፦በጥምቀት በዓል ላይ የሚታየው ስነ-ስርዓት፣ ውበትና ድምቀት አስደናቂ መሆኑን በአዲስ አበባ የጥምቀት በዓል ላይ የተገኙ የውጭ ሀገራት ጎብኚዎች ተናገሩ። የጥምቀት በዓል በጃንሜዳ የሀይማኖት አባቶች፣ ከፍተኛ የመንግስት ሀላፊዎች፣ የተለያዩ አገራት አምባሳደሮች፣ በርካታ ምዕመናን፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችና የውጭ ሀገር ጎብኚዎች በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል። በበዓሉ ላይ የታደሙና አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የውጭ ሀገራት ጎብኚዎች በመዲናዋ የጥምቀት በዓል አከባበር፣ በሕዝቡ ባህል፣ የሃይማኖት መከባበር እንዲሁም በከተማው ልማትና ውበት መደነቃቸውን ተናግረዋል። ከአሜሪካ በዓሉን ለመታደም ለመጀመሪያ ጊዜ የመጡት ሊያ ሮዝ በበዓሉ አከባበር ስነ-ስርዓትና ድምቀት መደነቃቸውን ገልጸዋል።   የጥምቀት በዓልን ለማክበር በርካታ ቁጥር ያለው ህዝብ ተሳትፎ ያለምንም ችግር በሰላም ተመልሶ መግባቱ በጣም የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል። በመዲናዋ በተመለከቱት ልማትና ውበት ፣ አረንጓዴና ውብ ስፍራዎች፣ የአየር ሁኔታ እንዲሁም የሰዎች እንግዳ አቀባበል አስደሳች መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያን ከሩቅ ሆነን የሰማነው እና አሁን በአካል መጥተን ስናየው በጣም የተለየ ነው ብለዋል። ሌላው አሜሪካዊ ደስቲን ፔንራድ በበዓሉ ላይ በመገኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸው፤ ኢትዮጵያ በጣም ልዩና ልትጎበኝ የምትገባ ሀገር መሆኗን ገልጸዋል።   በጉብኝታቸው ኢትዮጵያውያን እንግዳ ተቀባይና የበለጸገ ባህል እንዳላቸው መመልከታቸውን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በጣም የበለፀገ ባህል አላት ይህን እምቅ ሀብት ሌሎች ጎብኝዎች መጥተው እንዲመለከቱ እንደሚመክሩ ገልጸው እሳቸውም በድጋሚ መጥተው እንደሚጎበኙ ተናግረዋል። ከደቡብ ኮርያ የመጡት ሱጅን ፓርክ በጥምቀት በዓል ስነ-ስርዓት መደሰታቸውንና መደነቃቸውን ገልጸው፤ በድጋሚ ወደ ኢትዮጵያ የመምጣት ፍላጎት እንዳላችውም ተናግረዋል።   አዲስ አበባ ከተማ የአፍሪካ የነጻነትና የአንድነት ከተማ መሆኗን ለማየት ችለናል ሲሉም ተናግረዋል።
የኮሪደር ልማት የስራ ባህልን ከመለወጥ አልፎ አዲስ አበባን የቱሪዝም ማዕከል የማድረጉን እንቅስቃሴ ውጤታማ አድርጓል
Jan 19, 2026 52
አዲስ አበባ፣ጥር 11/2018 (ኢዜአ) ፦የኮሪደር ልማት የስራ ባህል እንዲለወጥ ከማድረግ ባሻገር አዲስ አበባን የቱሪዝም ማዕከል የማድረጉ እንቅስቃሴ ውጤታማ እንዲሆን አዎንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ የጥምቀት በዓልን ምክንያት በማድረግ በመዲናዋ የኮሪደር ፕሮጀክቶች ግንባታ ላይ እየተሳተፉ ላሉ ሰራተኞች ማዕድ አጋርተዋል።   ከንቲባ አዳነች በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኮሪደር ልማት የአዲስ አበባን ገጽታ በመቀየር አዲስ አበባን የቱሪዝም ማዕከል የማድረጉ ስራ ውጤታማ እንዲሆን አዎንታዊ አስተዋፅኦ እያበረከት ነው። የኮሪደር ልማቱ ከተማዋን ውብ፣ጸዱና ለነዋሪዎች ምቹ ከማድረግ ባለፈ የስራ ባህል እንዲቀየር መሰረት እየጣለ መሆኑንም ተናግረዋል።   በኮሪደር ልማት ላይ የተሳተፋችሁ ባለሙያዎች እና ሰራተኞች የዚህ ውጤት ምክንያት ናችሁ፤ ለዚህም ከተማ አስተዳደሩ ያመሰግናችኋል ብለዋል። በተለወጠ የስራ ባህል የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ስራዎች ገቢራዊ ማድረግ የትኩረት ማዕከላችን ነው ሲሉም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የጥምቀት በዓል አከባበር ልዩና ድንቅ ስርአት ያለው ነው
Jan 19, 2026 58
አርባምንጭ፤ጥር 11/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የጥምቀት በዓል አከባበር ልዩና ድንቅ ስርአት ያለው መሆኑን በአርባምንጭ በበዓሉ አከባበር ላይ የተገኙ የውጭ ሀገራት ጎብኚዎች ገለጹ። የነጭ ሳር ብሔራዊ ፓርክ፣የአባያና ጫሞ ሀይቆች፣ የ40ዎቹ ምንጮች፣ የአዞ ራንች፣ የባህላዊ የሸማ እና ጎጆ ቤት ጥበብ እና የሌሎች መስህቦች መገኛ የሆነችው አርባምንጭ ከተማ ዓመቱን ሙሉ ከፍተኛ ቁጥር ያለውን ጎብኚ ታስተናግዳለች። ከተለያዩ ሀገራት የመጡ ጎብኚዎች የዘንድሮውን የጥምቀት በዓል ከአርባምንጭ ከተማ ነዋሪዎች ጋር እያከበሩ ይገኛሉ። ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት አስተያየታቸውን የሰጡ የውጭ ሀገራት ጎብኚዎች እንደተናገሩት የኢትዮጵያ የጥምቀት በዓል አከባበር ልዩና ድንቅ ስርአት ያለው ነው፡፡ የጥምቀት በዓልን ከኢትዮጵያዊያን ጋር በማክበራችን ልዩ ደስታና የማይረሳ ትዝታ ፈጥሮልናል ብለዋል።   ፖላንዳዊው ጎብኚ ጃክ ቶርብሊዝ ኢትዮጵያዊያን የሚያከብሩትን የጥምቀት በዓል መመልከት በመቻሉ እጅግ ደስተኛ መሆኑን ተናግሯል። የኢትዮጵያ የጥምቀት በዓል ሃይማኖታዊ ስርዓቱና አከባበሩ ልዩና የትም የሌለ ድንቅ በዓል ነው ሲል ገልጿል። የዓለም ቅርስ የሆነው ኢትዮጵያ የጥምቀት በዓል ስርአት ተጠብቆ ለትውልድ ሊተላለፍ የሚገባ ነው ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል። ኢትዮጵያ የሰላም ምድር ናት ያለው ጎብኚው ሀገሪቱ በሁሉም ዘርፍ በፈጣን ዕድገት ላይ መሆኗን መመልከቱንም ነው የገለጸው። በዓለም ባሉ ከአንድ መቶ በላይ ሃገራት መዘዋወራቸውን የገለጹት ፊንላንዳዊቷ ኢቫ ፓሎጃርቢ በበኩላቸው፥ የኢትዮጵያዊያን የጥምቀት በዓል ልዩና ድንቅ መሆኑን ገልጸዋል።   ሁሉም በነጭ አለባበስ ደምቀው በአንድነት፣ በዝማሬና በቅዳሴ የሚፈጽሙት ሃይማኖታዊው ስርአት በጣም ደስ የሚያሰኝ ነው ብለዋል። የስነ ጽሑፍ ባለሙያ መሆናቸውን የገለጹት ጎብኚዋ ስለ ኢትዮጵያ ቅርስና ባህል በመጻፍ ለሌሎች እንደሚያስተዋውቁ ተናግረዋል። ሜክስኳዊው ካርሎስ ጎሚክሎጋ በበኩሉ፥ የጥምቀት በዓልን ጨምሮ የመስህብ ስፍራዎችን ለመመልከት ወደ ኢትዮጵያ መምጣቱን ገልጿል።   ልዩ የሆነውን የጥምቀት በዓል ኢትዮጵያ ውስጥ በማክበሩ ደስተኛ መሆኑን ገልጾ፥ እንግዳ አክባሪ የሆኑ ኢትዮጵያዊያን ባሳዩኝ ፍቅር እና አክብሮት ደስ ተሰኝቻለሁ ብሏል። ወደ ሀገሬ ስመለስ ሌሎች ጓደኞቼ የኢትዮጵያን ቅርስ፣የመስህብ ስፍራዎችና በዓላትን እንዲጎበኙ እነግራቸዋለሁ ብሏል። በዓለም የማይደሰስ ቅርስነት የተመዘገበው የኢትዮጵያ የጥምቀት በዓል በመላ ሃገሪቱ በሃይማኖታዊ ስርዓት በድምቀት እየተከበረ ይገኛል፡፡
የጎንደር የቅርስ ጥበቃና የልማት ስኬቶች የከተማዋን ገናና የሥልጣኔ ዘመን ዳግም ያበሰሩ ናቸው - ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ
Jan 18, 2026 116
አዲስ አበባ፤ ጥር 10/2018 (ኢዜአ)፦የጎንደር የቅርስ ጥበቃና የልማት ስኬቶች የከተማዋን ገናና የሥልጣኔ ዘመን ዳግም ያበሰሩ መሆናቸውን ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ ገለጹ። ለጎንደር ከተማ ማንሠራራት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የምስጋና እና ዕውቅና መርሃ ግብር በዓፄ ፋሲለደስ አብያተ መንግሥታት ቅጥር ግቢ ተካሂዷል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ፤ ለጎንደር ከተማ ልማት አስተዋጽኦ ያበረከቱ ሁሉ የላቀ ምስጋና ይገባቸዋል ብለዋል። የጎንደር ሕዝብ ለኢትዮጵያ አንድነት ካለው ቀናኢነትና ታታሪነት ባሻገር፣ ያደረጉለትን ማመስገን ባህሉ መሆኑን ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለዓፄ ፋሲለደስ አብያተ መንግሥታት ዕድሳትና ለጎንደር ገናና የታሪክ ሥልጣኔ መነሳት ላበረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦ ምስጋና አቅርበዋል።   በአሁኑ ወቅት ጎንደር በትውልድ ትንሣኤ ዘመን ላይ መሆኗን ገልጸው፤ የጎንደር ገናና የሥልጣኔ ታሪክ የኪነ-ጥበብ፣ የትምህርት፣ የዕድገትና የልማት መገለጫዋ ነው ብለዋል። ይህ እንዲሆን በጎንደር ከተማ የልማትና የቅርስ ዕድሳት ስኬት ለተጨነቁና ላሰቡ፣ በትግበራ ሂደቱና በፍጻሜው ደስታን ላገኙ አካላት ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። በቀጣይም የጎንደርን ዕድገትና ብልጽግና በማስቀጠል፣ በቅርስ ጥበቃና አዳዲስ ልማትን በማንበር ሕዝብን ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚያስፈልግም አጽንኦት ሰጥተዋል።   የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፤ "ጎንደር ትሞሸር" በሚል ለቀረበው ጥሪ ሁሉም በጎ ምላሽ በመስጠት ከተማዋ ውብና ምቹ እንድትሆን ላበረከቱት አስተዋጽኦ አመስግነዋል። ጎንደርን ይበልጥ ውብ፣ ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ እና የቱሪስት መዳረሻነቷን ለማጠናከር ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ዳግም ጥሪ አቅርበዋል። የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው፤ በአሁን ወቅት የጎንደር የሥልጣኔ ዘመን በብልጽግና መንገድ እያንሠራራ ነው ብለዋል።   በጎንደር ዓፄ ፋሲለደስ አብያተ መንግሥታት ዕድሳትና የልማት ስኬቶች ድጋፍና አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የላቀ ምስጋና አቅርበዋል።   በዕውቅና መርሃ ግብሩ ላይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የጠቅላይ ሚኒስትር የማኅበራዊ ጉዳይ አማካሪ ሚኒስትር ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረትን ጨምሮ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።
አስተዳደሩ የዜጎችን ኑሮ የሚያሻሽሉ ሰው ተኮር ተግባራትን አጠናክሮ ይቀጥላል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jan 18, 2026 115
አዲስ አበባ፤ ጥር 10/2018 (ኢዜአ)፦‎ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል የሚያከናውናቸውን የሰው ተኮር ተግባራት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በልደታ ክፍለ ከተማ ወረዳ 8 መካኒሳ አቦ ማዞሪያ አካባቢ ቀደም ሲል በጉሊት ንግድ ላይ ተሰማርተው ለቆዩ እናቶች የተገነቡ ዘመናዊ የንግድ ሱቆችን አስረክበዋል፡፡   ከንቲባ አዳነች በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ እነዚህ እናቶች ቀደም ሲል ፀሀይ፣ አቧራና ዝናብ እየተፈራረቀባቸው ሥራቸውን በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ በማከናወን ቤተሰቦቻቸውን ሲያስተዳድሩ እንደቆዩ አስታውሰዋል። የኮሪደር ልማት ከመሰራቱ በፊት ጉሊት ቦታ የሆነውን በመቀየር ዘመናዊ የመሸጫ ቦታ መሰራቱን ጠቅሰው፤ በከተማዋ እየተካሄደ ያለው ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ የዜጎችን የሥራ አካባቢ ምቹና ዘመናዊ ማድረጉን ገልጸዋል።   በከተማዋ የሚከናወኑ ማንኛውም የልማት ስራዎች ሰው ተኮርና የነዋሪውን ሕይወት የሚቀይሩ መሆናቸውን ከንቲባዋ ተናግረዋል። ዛሬ የመስሪያ ቦታ የተረከቡ እናቶችም ለሽያጭ የሚያቀርቡትን ምርት በቀላሉ እንዲያገኙ ከላፍቶ ገበያ ማዕከል ጋር የገበያ ትስስር እንደተፈጠረላቸው አስታውቀዋል።   እናቶች በምቹ ሁኔታ እንዲነግዱና የአካባቢው ማኅበረሰብም ምርቶችን ከእነዚሁ እናቶች በመግዛት እንዲያበረታታቸው ጥሪ አቅርበዋል።
የገበታ ለትውልድ ሥራ የመጀመሪያው መዳረሻ የሆነው ደንቢ ኢኮ ሎጅ በይፋ ተመረቀ
Jan 18, 2026 104
አዲስ አበባ፤ ጥር 10/2018 (ኢዜአ)፦‎ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የገበታ ለትውልድ ሥራ የመጀመሪያው መዳረሻ የሆነው እና በ36.7 ሔክታር የጥብቅ ደን እና የተፈጥሮ ኃብት ስጦታ የተዘረጋው ደንቢ ኢኮ ሎጅ በይፋ ተመርቋል።   ኢኮ ሎጁ የሀገራችን የቱሪዝም ዘርፍ ባለፉት ሰባት ዓመታት ዘላቂነትን፣ የቅርስ ሀብትን እና ለዘመናት የሚዘልቅ ዓለም አቀፍ ደረጃን የመጠበቅ ዕድል መፍጠርን በማዋሃድ ምን ያህል እንደተለወጠ ማሳያ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ገልጿል። የገበታ ለትውልድ ሥራ ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቁ መዳረሻዎችን በማልማት የሀገራችንን እምቅ አቅም ለማውጣት የሚደረገው የሰፊው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ስትራቴጂ አካል ነውም ብሏል።   በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተጀመረው ይኽ ሥራ በስኬት ከተተገበሩት የገበታ ለሸገር እና ገበታ ለሀገር መርሐ-ግብሮች የቀጠለ እና ሥራዎቹን ወደአዳዲስ አካባቢዎች የወሰደ ሲሆን የተፈጥሮ ውበትን፣ የባሕል ቅርስን እና ዘላቂ ልምድን በማቀናጀት የተከናወነም መሆኑ ተመላክቷል።   እነዚህ ሥራዎች የከተማ እና ተፈጥሯዊ መዳረሻዎችን ወደ ሳቢ የቱሪዝም ማዕከልነት የለወጡ መሆናቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት በማህበራዊ ትስስር ገጹ አስታውቋል።
የግብር ከፋዩ ለሀገር ዕድገት ያለው ቁርጠኝነት ማደግ ስኬታማ ለውጥ እንዲመዘገብ አግዟል- ሚኒስትር ዓይናለም ንጉሤ
Jan 17, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ ግብር ከፋዩ የሚከፍለው ግብር ለሀገር ዕድገት እንደሚውል ያለው ግንዛቤና ታክስ የመክፈል ቁርጠኝነት ማደግ ስኬታማ የታክስ አሰባሰብ እንዲኖር ማገዙን የገቢዎች ሚኒስትር ዓይናለም ንጉሤ ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ''የፋይናንስ እመርታ በኢትዮጵያ'' በሚል ሐሳብ በተካሄደ ኮንፈረንስ ላይ የገቢዎች ሚኒስትር ዓይናለም ንጉሤ ገለጻ አድርገዋል። ሚኒስትሯ የታክስ አሥተዳደር ሪፎርም ለኢኮኖሚ ዕድገት እና ቀጣይነት በሚል ርዕሰ ጉዳይ ባቀረቡት ገለጻ፤ የታክስ አሥተዳደር አገልግሎት አሰጣጥን ማሻሻልና የማስፈጸም ዐቅምን ማጠናከር፣ ዘመናዊ የታክስ አሥተዳደር ሥርዓት መገንባት፣የታክስ ሕግ ተገዥነትን ማረጋገጥ እና ዘላቂ የገቢ ዕድገት ማረጋገጥ በሚሉት ዐበይት ጉዳዮች ላይ ሪፎርሙ መከናወኑን አንስተዋል። ከላይ በተገለጹት ጉዳዮች ላይ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣትም በሪፎርሙ ወቅት የፖሊሲ እና የሕግ ማሻሻዎች መደረጋቸውን ጠቁመው፥ እነዚህን ለመፈጸምም የአሠራር ማሻሻያዎች ተደርገዋል ብለዋል። ቅርንጫፎች ማስፋፋትን ጨምሮ ከፌደራል እስከ ክልል ባሉ ባለድርሻ አካላት ዘንድ ስኬታማ ተግባራት ለማስመዝገብ እንዲቻል የዐቅም ግንባታ ሥራዎች መከናወናቸውንም ጠቅሰዋል። እንደ ሀገር የተጣጣመ የታክስ አሥተዳደር ሥርዓት እንዲኖር ጥረቶች መደረጋቸውንም አመላክተዋል። የዲጂታል ሥርዓቶችን በመዘርጋት ለግብር ከፋዮች ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር አንጻር ስኬታማ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተው፤ ለአብነትም መሠረታዊ የሚባሉ የዲጂታል ፕላት ፎርሞች መዘርጋታቸውን ጠቅሰዋል። በዚህም መሠረት ግብር ከፋዩ በየቢሮው መሄድ ሳይጠበቅበት ኢ-ፋይል እና ኢ-ፔይ የሚያደርግበትን ሥርዓት ዘርግተናል ነው ያሉት። በሌላ በኩል በኢንሳ አማካኝነት ለምቶ በቅርቡ ወደ ሥራ እያስገባነው ባለው የኤሌክትሮኒክ ኢንቮይሲንግ ሲስተም በትራንዛክሽን ደረጃ ወደ 291 ቢሊየን ብር ግብይት ተካሂዶበታል ብለዋል። ይህም ከሐሰተኛ ደረሠኝ፣ ከውሳኔ አሰጣጥ፣ ከመረጃ አጠቃቀም እና ተያያዥ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ያሉ ችግሮችን የሚቀርፍ መሆኑን አስገንዝበዋል። ከጉምሩክ አገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘም አሁን ላይ የወጪና ገቢ ንግድን ከማሳለጥ አንጻር በአንድ መስኮት አገልግሎት ከ80 በላይ ተቋማት በአንድ ማዕከል አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። በሌላ በኩል ኢኮኖሚውን በዘላቂነት የሚደግፍ ወደ ሉዓላዊነት የሚወስደን ገቢ በሀገር ውስጥ መመንጨት አለበት በሚል የተከናወነው ሥራ የሪፎርሙን ስኬት አሳይቷል ነው ያሉት። በዚህም መሠረት በ2011 የበጀት ዓመት የፌደራል መንግሥት 198 ቢሊየን ብር ታክስ መሰብሰቡን አውስተው፤ በ2017 ደግሞ 900 ቢሊየን ብር መሰብሰቡን ገልጸዋል። በተያዘው ዓመት የመጀመሪያ አጋማሽ ደግሞ 907 ቢሊየን ብር መሰብሰቡን ገልጸው፤ ይህ አሃዝ ከዕቅዳችን አንጻር ወደ 68 ቢሊየን ብር ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት አንጻርም የ258 ቢሊየን ብር ብልጫ ማሳየቱን አንስተዋል። ይህም በየደረጃው ያሉ አካላት ድጋፍ፣ የግብር ከፋዮች ሀገርን ለመለወጥ ያለባቸውን ኃላፊነት ለመወጣት ያላቸው ቁርጠኝነት ውጤት መሆኑን በአጽንኦት ገልጸዋል። ከክልሎች አኳያም በ2011 የታክስ ገቢ 79 ቢሊየን ብር ብቻ እንደነበር አውስተው፤ በ2017 ደግሞ 543 ቢሊየን ብር መሰብሰባቸውን ተናግረዋል። በተያዘው የበጀት ዓመት እንደ ሀገር ከ2 ነጥብ 1 ትሪሊየን ብር በላይ ታክስ ለመሰብሰብ መታቀዱን እና ባለፉት ስድስት ወራት 1 ነጥብ 17 ትሪሊየን ብር ታክስ መሰብሰቡን አስታውቀዋል።
የኢኮኖሚ ሪፎርሙ በዘርፉ የጎላ ሚና ያላቸው ቁልፍ ተቋማትን ወልዷል- ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ
Jan 17, 2026 71
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦ የለውጡ መንግሥት ያከናወነው የኢኮኖሚ ሪፎርም በኢኮኖሚ ረገድ ቁልፍ ሚና ያላቸው ተቋማት መውለዱንና የኢኮኖሚ ዕድገቱንም ማቃናቱን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ''የፋይናንስ እመርታ በኢትዮጵያ '' በሚል ሐሳብ በተካሄደ ኮንፈረንስ ላይ የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ ገለጻ አድርገዋል። በገለጻቸውም፤ከሰባት ዓመታት በፊት ኢኮኖሚውን የገጠሙት ዋና ዋና የማክሮ ፊሲካል ተግዳሮቶችን አንስተዋል። እነዚህ ተግዳሮቶችም፤ ከፍተኛ የዋጋ ንረት፣ የማክሮ ኢኮኖሚ መዛባት፣ ዘላቂና አስተማማኝ የፊሲካል ቁመና አለመኖር፣ ከፍተኛ የዕዳ ጫና፣ የውጭ ምንዛሪ እጥረት እና የገበያ አለመረጋጋት መሆናቸውን አብራርተዋል። ስለዚህ ይህን የማክሮ ኢኮኖሚ ስብራት ለመጠገን ላለፉት ሰባት ዓመታት መንግሥት፤ በመጀመሪያው እና በሁለተኛው የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርም ሊከሰት የነበረውን የማክሮ ፋይናንሻል ቀውስ አስቀርቷል ብለዋል። በዚህም ጠንካራ ዕድገትን አስመዝግቦ በሁሉም የማክሮ ኢኮኖሚ አመላካቾች (ኢንዲኬተሮች) ወደ ተሻለ ቁመና ለመሻገር ተችሏል ነው ያሉት ሚኒስትሩ። በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ፈጣን እድገት እያስመዘገቡ ካሉ ሀገራት አንዷ ልትሆን ትችላለች ነው ያሉት። የኢኮኖሚ ሪፎርሙ ጠንካራ ተቋማት የተፈጠሩበት መሆኑን በአጽንኦት ያነሱት ሚኒስትሩ፤ ስለዚህ ከተቋማት ግንባታ አንጻርም በኢኮኖሚ ረገድ ቁልፍ ሚና ያላቸው ተቋማትን የወለደ ሪፎርም ነው ብለዋል። በተጨማሪም የኢኮኖሚ ዕድገቱን ያቃና ሪፎርም መሆኑን ጠቁመው፤ በዚህም በርካታ ውጤቶች መገኘታቸውን አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ሎተሪ አገልግሎት በዲጂታል አማራጭ በመላ ሀገሪቱ ተደራሽነቱን እያሰፋ ነው
Jan 17, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሎተሪ አገልግሎት በዲጂታል አማራጭ በመላ ሀገሪቱ ተደራሽነቱን እያሰፋ መሆኑን አገልግሎቱ ምክትል ዋና ስራ አስፈጻሚ ሙሉጌታ ታደሰ ገለጹ። በሀገሪቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ተግባራዊ የተደረገው 60 ሚሊየን ብር ተሸላሚ የሚያደርገው ዲጂታል ሎተሪ ዕጣ በኢትዮጵያ ሎተሪ አገልግሎት እድል አዳራሸ ወጥቷል። በእጣ አወጣጥ ስነ ሰርዓቱ ላይ የመንግስት ተቋማት ሀላፊዎች፣ ባለድርሻ አካላትና ታዛቢዎች ተገኝተዋል።   የ60 ሚሊየን ብር ዕጣው 6361547፤ 20 ሚሊየን ብር ተሸላሚ የሚያደርገው እጣ 5681025 እንዲሁም 10 ሚሊየን ብር ተሸላሚ የሚያደርገው ዕጣ 7699884 እንዲሁም ማስተዛዘኛ ቁጥር 4 ሆኖ ወጥቷል። በመርሃ ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ ሎተሪ አገልግሎት ምክትል ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሙሉጌታ ታደሰ እንደተናገሩት፤ የ60 ሚሊየን ብር ዲጂታል ሎተሪ በሽልማት ከፍተኛው መሆኑና ለመጀመሪያ ጊዜ በዲጂታል ብቻ መቅረቡ ልዩ ያደርገዋል። ደንበኞች በየትኛውም ተንቀሳቃሽ ስልክ፣ በፖዝ ማሽን፣ በድረ ገጽና በተለያዩ የዲጂታል አማራጮች መሳተፍ መቻላቸውን ገልጸዋል። ይህም የሎተሪን ስራ ወጪ ቆጣቢ ፈጣንና ተደራሽ ማድረጉን ገልጸው፤ ደንበኞች በፍጥነትና በቀላሉ እንዲሳተፉ አስችሏል ብለዋል።   በኢትዮጵያ ሎተሪ አገልግሎት የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ቴድሮስ ነዋይ በበኩላቸው፤ ዲጂታል ሎተሪ ሙሉ ለመሉ በዲጂታል መከናወኑ አገልግሎቱን ቀልጣፋ ማድረግ መቻሉን ጠቁመው፤ አሰራሩም ለደንበኞች ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንና ተሸላሚዎችን በቀላሉ ለማግኘት መቻሉን ተናግረዋል። በታምኮል ሶፍትዌር ሶልዩሽንስ የሳይበር ደህነነት ክፍል ሀላፊ አንማው ቃሬ የሎተሪ አገልግሎትን ለማዘመንና ዲጂታላይዝ ለማድረግ በጋራ እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።   ይህም የሎተሪ አገልግሎትን ከዝግጅት ጀምሮ እስከ ሽልማት ማውጣትና ደንበኞችን መለየት ደረጃ ድረስ በዲጂታል ለማከናወን አስችሏል ብለዋል።    
የብዝሀ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራው በሚፈጥረው የሥራ ዕድል ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል
Jan 17, 2026 67
ሆሳዕና፤ ጥር 9/2018(ኢዜአ)፡-የብዝሀ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራው ለሀገር ውስጥ የሥራ ስምሪት በፈጠረው የሥራ ዕድል ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የተጀመረው ሥራ እንደሚጠናከር የሥራ እና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ለኢዜአ እንደገለጹት የብዝሀ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራው ለሀገር ውስጥ የሥራ ስምሪት የፈጠረውን ዕድል ለዜጎች ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቷል፡፡ በበጀት ዓመቱ 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ግብ ተጥሎ ባለፉት 6 ወራት በግብርና ፣ በኢንዱስትሪና በአገልግሎት ዘርፍ 2 ነጥብ 6 ሚሊዮን ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ እድል ለመፍጠር መቻሉን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ውስጥ 2 ነጥብ 2 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎችን በብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራው በተፈጠረ የሥራ እድል በሀገር ውስጥ የሥራ ስምሪት ተጠቃሚ ለማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ቀሪው የውጪ ሀገር የሥራ ስምሪትና ቴክኖሎጂን በመጠቀም በርቀት የተፈጠረ የሥራ ዕድል መሆኑንም አስረድተዋል። እንደ ሚኒስትሯ ገለጻ በሥራ ዕድል ፈጠራ ከልየታ እስከ ሥራ ስምሪት ድረስ ያለው ተግባር የተከናወነው የኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ አጠቃቀምን መሰረት ባደረገ መልኩ ነው፡፡ ለዜጎች የተፈጠረው የሥራ ዕድል ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራን ታሳቢ ባደረገ መልኩ በመሆኑ በሁሉም ክልሎች በዘርፉ ተጨባጭ ለውጥ እየተመዘገበ መምጣቱንም ጠቅሰዋል። በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ስድስት ወራት በተከናወኑ ተግባራት የተገኙ ውጤቶችን አጠናክሮ በማስቀጠል ለማህበረሰቡ ተጠቃሚነት መረጋገጥ በትኩረት እንደሚሰራም ገልጸዋል።        
በክልሉ ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰጠው ትኩረት ባለሀብቶች በተለያዩ መስኮች እንዲሰማሩ ምቹ ምህዳር ፈጥሯል
Jan 17, 2026 89
ወላይታ ሶዶ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰጠው ትኩረት ባለሀብቶች በተለያዩ መስኮች እንዲሰማሩ ምቹ ምህዳር መፍጠሩን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ተናገሩ። የወላይታ ሶዶ ከተማ ፈጣን ዕድገት ለኢንቨስትመንት ተመራጭ መዳረሻ እያደረጋት መምጣቱም ተመላክቷል። ርዕሰ መስተዳድሩ በወላይታ ሶዶ ከተማ በአንድ ባለሀብት ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነባ ሆቴልን ዛሬ መርቀው ከፍተዋል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህን ወቅት እንዳሉት ለከተሞች እድገትና ለሆቴል ኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ የግል ባለሀብቶች ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። በክልሉ ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰጠው ትኩረት ባለሀብቶች በተለያዩ መስኮች ተሰማርተው ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ ምህዳር መፈጠሩን ገልጸዋል። የወላይታ ሶዶ ከተማ ፈጣን ዕድገት ለኢንቨስትመንት ተመራጭ መዳረሻ እያደረጋት መሆኑንም አቶ ጥላሁን ጠቁመዋል። ዛሬ የተመረቀው "ታከለ ሆቴል"ም በፈጣን የልማት ጉዞ ላይ ለምትገኘው ወላይታ ሶዶ ከተማ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆንና ለሌሎች ባለሀብቶችም መነቃቃት እንደሚፈጥር ገልጸዋል። የሆቴሉ ባለቤት ከትንሽ ንግድ ሥራ ጀምረው ለትልቅ ደረጃ መድረሳቸው ለሌሎችም ተሞክሮ ይሆናል ሲሉም አቶ ጥላሁን ተናግረዋል፡፡ በክልሉ በአገልግሎት፣ በግብርና፣ በኢንዱስትሪና በሌሎችም የኢኮኖሚ ዘርፎች ለተሰማሩ ባለሀብቶች የቅርብ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ ጠቁመው፣ ሌሎች ባለሀብቶች ያለውን ምቹ ምህዳር ተጠቅመው ወደክልሉ እንዲመጡ ጥሪ አቅርበዋል።   የሆቴሉ መመረቅ ለኮንፈረንስ ቱሪዝም አበርክቶው የጎላ መሆኑን የተናገሩት የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማርያም በበኩላቸው በከተማዋ ዕድገት ላይ የግል ባለሀብቶች ሚና የላቀ መሆኑን ተናግረዋል። በከተማዋ መሰረተ ልማቶችን በማሟላት ኢንቨስትመንት ለመሳብ በተሰራው ሥራ በርካታ ባለሀብቶች የልማት ጥያቄ እያቀረቡ መሆኑን ጠቁመዋል። ለሆቴሉ ግንባታ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉንና ከ150 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ጊዜያዊና ቋሚ የሥራ ዕድል መፈጠሩን የተናገሩት ደግሞ የሆቴሉ ባለቤት አቶ ታከለ ቦሼ ናቸው። በክልሉ ያለው ምቹ የኢንቨስትመንት ምህዳር እና በየደረጃው የተደረገላቸው ድጋፍ ለሥራቸው ውጤታማነት አስተዋጸኦ ማድረጉን የገለጹት ባለሀብቱ፣ ስለተደረገላቸው ሁለንተናዊ ድጋፍም አመስግነዋል።   በሆቴሉ ምረቃ መርሃ ግብር ላይ የክልሉ፣ የዞንና የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎች እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው አካላት ተገኝተዋል።
አርሶ አደሩ የእርሻ መሬት ይዞታ ማረጋገጫ መያዙ ሀብቱን በአግባቡ ለመጠቀም ያስችለዋል
Jan 17, 2026 99
አዳማ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፡- አርሶ አደሩ የእርሻ መሬት ይዞታ ባለቤትነት ማረጋገጫ ካርታ መያዙ ሀብቱን በአግባቡ ለማልማትና ለመጠቀም ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የኦሮሚያ ክልል መሬት ቢሮ አስታወቀ። በአዳማ ከተማ አሥተዳደር ሥር ለሚገኙ ከ24 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች የእርሻ መሬት የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ የመስጠት መርሐ-ግብር ተከናውኗል።   የቢሮው ኃላፊ መሰረት አሰፋ በዚሁ ወቅት፤ በገጠር የመሬት ይዞታ ባለቤትነትን ለማረጋገጥ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ለአርሶ አደሩ መሰጠቱ ሀብቱን በአግባቡ ለማልማትና ለመጠቀም ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ብለዋል። ለአዳማ ከተማ አርሶ አደሮች ሕጋዊ መብትና ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ ዲጂታል ካርታ መሰጠቱም የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም አርሶ አደሩ በግሉም ሆነ በማኅበር ተደራጅቶ መሬቱን እንዲያለማ ከባንኮች ብድር እንዲያገኝበትና ወደ ኢንቨስትመንት ማደግ እንዲችል የሚያግዝ መሆኑንን አስገንዝበዋል። በክልሉ ከተሞች የመሬት ካዳስተር ሥርዓት ዕውን በማድረግ በመሬት ሀብት አሥተዳደርና አጠቃቀም ዙሪያ የነበሩ ችግሮች እየተቀረፉ መሆኑንም አረጋግጠዋል።   የአዳማ ከተማ አሥተዳደር ከንቲባ ኃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው፤ መሬትን በቴክኖሎጂ ለመምራት፣ ለማሥተዳደርና አገልግሎት ላይ ለማዋል በተደረገው ጥረት በከተማዋ ውጤት መምጣቱን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት አዲስ ወደ ከተማዋ የተቀላቀሉ ቀበሌዎች ዘመናዊ የመሬት አሥተዳደር አሠራር እንዲከተሉ እየተሠራ መሆኑንም አስታውቀዋል። በዚህም መሠረት አርሶ አደሩ ባለው የመሬት ሀብት ላይ ሕጋዊ ባለይዞታነትና መብት እንዲኖረው ለማድረግ ዲጂታል የካዳስተር ካርታ እንዲያገኝ መደረጉን ጠቁመዋል። ካርታው አርሶ አደሩ ይዞታውን በባለቤትነት እንዲያለማና አማራጭ የፋይናንስ ምንጮች እንዲያገኝ የሚያስችል ከመሆኑም ባለፈ፤ በፕላኑ መሠረት አካባቢውን እንዲያለማ ቁልፍ ሚና አለው ብለዋል።   የተሰጠን የይዞታ ማረጋገጫ መሬቱ የእኛ ስለመሆኑ ሕጋዊ መብት ያገኘንበት ነው ያሉት ደግሞ በአዳማ ከተማ የቶርበን ኦቦ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ተንኮሉ ለታ ናቸው። ወደ ከተማ ስንቀላቀል መሬታችን ይወሰድብናል የሚል ስጋት ነበረን፤ ይሁን እንጅ አሁን ለመሬታችን የባለቤትነት ካርታና ሕጋዊ መብት በማግኘታችን ስጋታችን ትክክል እንዳልሆነ አረጋግጠናል ብለዋል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አርሶ አደር በዳዳ ጂማ በበኩላቸው፤ መሥተዳድሩ ለመሬት ሀብታችን ሕጋዊ የይዞታ ማረጋገጫ ሠነድ በመስጠቱ ደስተኞች ነን ብለዋል።
በስራ ዕድል ፈጠራና በክህሎት ልማት የተጀመሩ አበረታች ውጤቶች ወደ ሁሉም አካባቢዎች እንዲሰፉ ይደረጋል
Jan 17, 2026 81
ድሬደዋ፣ ጥር 9/2018(ኢዜአ)፡- በስራ ዕድል ፈጠራና በክህሎት ልማት የተጀመሩ አበረታች ውጤቶች ወደ ሁሉም አካባቢዎች እንደሚሰፉ የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ገለጸ። የሚኒስቴሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በሶማሌና በሐረሪ ክልሎች እንዲሁም በድሬደዋ አስተዳደር የመስክ ጉብኝት በማድረግ በድጋፍና ክትትል የተስተዋሉ ጠንካራ ጎኖችን ለማስቀጠል እና ክፍተቶችን ተቀናጅቶ ለመፍታት በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ምክክርም ተደርጓል።   በዚሁ ጊዜ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ደኤታ አቶ ዳንኤል ተሬሳ እንዳሉት፤ ባለፉት አራት ዓመታት አዳዲስ እሳቤዎችን ወደ ተግባር በመቀየር በክልሎችና ከተማ አስተዳድሮች በስራ ዕድል ፈጠራና በክህሎት ልማት ላይ የተከናወኑ ስራዎች ውጤታማ ናቸው። በተቋማት ግንባታ እንዲሁም የአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነት ለማጠናከር በተሰሩ ስራዎችም የተሻለ ውጤት መገኘቱን ተናግረዋል። ባለፉት አራት ዓመታት በተሰሩ ስራዎች ከ16ሚሊዮን በላይ የስራ ዕድል መፈጠሩን አንስተው የተገኘው ውጤት ካለው የስራ ፍላጎትና በየአመቱ ወደ ገበያ ከሚቀላቀለው የሰው ኃይል አንፃር ይበልጥ ተቀናጅቶ መትጋት እንደሚጠይቅ ገልጸዋል። በዘርፉ ላይ በተቀናጀ መንገድ በመደጋገፍ እና በመናበብ የሚሰሩ ስራዎች እንደ አገር የተቀመጡትን የብልፅግና ትልሞች ለማሳካት መሠረታዊ መሆናቸውንም አስረድተዋል። በአመት ሁለት ጊዜ በክልሎችና በከተማ አስተዳድሮች በተቋማት ግንባታ፣ በክህሎት ልማት፣ በስራ ዕድል ፈጠራና በአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነት ላይ የሚካሄደው የድጋፍና የክትትል ስራ የተጀመሩ ስራዎችን በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም ገልጸዋል። በተለይም ስራ ዕድል ፈጠራና በክህሎት ልማት የተጀመሩ አበረታች ውጤቶች ወደ ሁሉም አካባቢዎች እንዲሰፉ ይደረጋል ነው ያሉት።   የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር በበኩላቸው የ10 ዓመታት መሪ ውጥኖችን መነሻ በማድረግ በስራና ክህሎት ዘርፍ እየተከናወኑ የሚገኙት አበረታች ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። በምስራቅ ተጎራባች ክልሎች ላይ የተካሄደው ድጋፋዊ ክትትልና ውይይት በመደጋገፍና በመቀናጀት የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የሚያስችል መሆኑንም አንስተዋል። በድሬዳዋ ወጣቱን ክህሎት መር ስልጠና በማስታጠቅ የስራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ የተጀመረው ውጤታማ ስራም ተስፋ ሰጪ መሆኑን ተናግረዋል። የተካሄደው የመስክ ግምገማና ውይይት ችግሮችን ለማረም ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የገለፁት ደግሞ የድሬዳዋ አስተዳደር የስራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሮቤል ጌታቸው ናቸው።   ዛሬ በተካሄደው ውይይት ላይ የስራና ክህሎት ሚኒስቴር የድጋፍና ክትትል ቡድን አባላትና አመራሮች፣ የሐረሪ እና የሶማሌ ክልሎች እንዲሁም የድሬደዋ የስራና ክህሎት አመራሮችና የማኔጅመንት አባላት ተሳታፊ ሆነዋል።
በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸው ራሳቸውን እንዲችሉ እየተደረገ ነው
Jan 17, 2026 87
ጅማ፤ ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጎች በከተማ ማስዋብ ዘርፍ የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸው ራሳቸውን እንዲችሉ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ከተማ ልማት እና ቤቶች ቢሮ ገለጸ። በጅማ ከተማ በልማታዊ ሴፍቲኔት ታቅፈው በከተማ ማስዋብ ሥራ ተሰማርተው የነበሩ ከ3 ሺህ በላይ አባዎራዎች እና እማዎራዎች ራሳቸውን ችለው ወደ ሥራ ተሸጋግረዋል። በዚሁ ወቅት የኦሮሚያ ክልል ከተማ ልማት እና ቤቶች ቢሮ ምክትል ኃላፊ ብርሃኑ በቀለ፤ የክልሉ ከተሞች መኖሪያ ብቻ ሳይሆኑ የማምረቻ ስፍራ እንዲሆኑ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም መሠረት በዝቀተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጎች በልማታዊ ሴፍቲ ኔት ታቅፈው በተለያዩ የከተማ ጽዳት እና ውበት ሥራዎች ተሰማርተው ኑሯቸውን እንዲያሻሽሉ እየተደረገ ነው ብለዋል። እነዚህ ዜጎች ከሚያገኙት ገቢ በመቆጠብ በሚፈልጉት የሥራ ዘርፍ እንዲሰማሩ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ ዛሬ በጅማ ከተማ የተሸጋገሩት የዚሁ ማሳያ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በከተሞች ያለውን የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ችግሮች ከከተማ ልማት ጋር በማስተሳሰር መፍትሔ ለመስጠት የተጀመረው ሥራ እንደሚጠናከርም አረጋግጠዋል።   የጅማ ከተማ ምክትል ከንቲባ አሥራት እሸቴ በበኩላቸው፤ በልማታዊ ሴፍቲኔት አማካኝነት በከተማ ውበት ሥራዎች ተሰማርተው የቆዩ 3 ሺህ 90 አባዎራዎች ወደ አምራችነት ተሸጋግረዋል ብለዋል። በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ የሚገኙ ወገኖች የሥራ እና የቁጠባ ባህልን በማጎልበት አምራችነታቸውን የማሳደግ ሥራ በትኩረት እንደሚከናወንም አመላክተዋል።   በመርሐ-ግብሩ ታቅፈው ዛሬ ከተሸጋገሩት መካከል አስረስ መንግሥቱ፤ ከገቢያቸው በመቆጠብ የራሳቸውን እና የቤተሰባቸውን ኑሮ ለመለወጥ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። በተመቻቸላቸው ዕድል ከትንሽ ንግድ ጀምረው አሁን ጥሩ ገቢ ማግኘት መጀመራቸውን የተናገሩት ደግሞ አስናቀች በቀለ ናቸው።
የጥምቀት በዓልን የሚያደምቁ ባህላዊ አልባሳትና ጌጣጌጦች ለገበያ ቀርበዋል-ነጋዴዎችና ሸማቾች
Jan 17, 2026 70
አዲስ አበባ፤ጥር 9/2018 (ኢዜአ)፡- የከተራ እና የጥምቀት በዓል አስመልክቶ የኢትዮጵያን ጥንታዊ ታሪክና እሴት የሚያንጸባርቁ የባህል አልባሳትና ጌጣጌጦች ለገበያ መቅረባቸውን ነጋዴዎችና ሸማቾች ገለጹ። በዓሉ ከሃይማኖታዊ ይዘቱ ባለፈ የሀገር በቀል የዕደ-ጥበብ ውጤቶች የሚያስተዋውቁበትና ለዘርፉ ነጋዴዎች ከፍተኛ የገቢ ምንጭ የሚገኝበት አጋጣሚ ሆኗል። ኢትዮጵያ ረጅም ዘመናትን ያስቆጠሩ በርካታ ባህላዊ እና ሃይማኖታዊ እሴቶች ያሏት ሀገር ስትሆን፤ ከነዚህም መካከል በአደባባይ በድምቀት የሚከበረው የጥምቀት በዓል የኢትዮጵያውያን የአብሮነትና የማንነት መገለጫ ተደርጎ ይወሰዳል። የጥምቀት በዓል የሀገርን ባህልና ታሪክ ለዓለም በማስተዋወቅ ረገድ ያለው ሚና ከፍተኛ ሲሆን በከተማዋ የታየው የባህል አልባሳትና ጌጣጌጦች የንግድ እንቅስቃሴ ለሀገራዊ ኢኮኖሚውና ለዘርፉ ነጋዴዎች ተስፋ ሰጪ መሆኑ ተመላክቷል።   የሀገር ባህል ልብሶች ዲዛይነርና አቅራቢ ወይዘሮ ፋናዬ ነጋ እንደገለጹት፤ የጥምቀት በዓልን በድምቀት ለማክበር በርካታ የመዲናዋ ነዋሪዎችና ጎብኚዎች ባህላዊ አልባሳትን በመግዛት ላይ ናቸው ብለዋል። የኢትዮጵያ ባህላዊ አልባሳት ዘመናዊ ዲዛይኖችን ተላብሰው እየተዘጋጁ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ይህም ለበዓሉ ድምቀት ከመስጠት ባለፈ የሀገር ውስጥ የጨርቃጨርቅ ውጤቶች የገበያ ተፈላጊነት እንዲጨምር እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። የጥምቀት በዓል ለጌጣጌጥና አልባሳት ነጋዴዎች ትልቅ የኢኮኖሚ መነቃቃትን መፍጠሩን ጠቁመዋል፡፡   ወይዘሪት ሰላም ከድር በበኩሏ፤በዓሉን ለማድመቅ የሚቀርቡት አልባሳትና ጌጣጌጦች የኢትዮጵያን ታሪክና የጥበብ ጥራትን ለዓለም የሚያስተዋውቁ መሆናቸውን ገልጻለች፡፡ በአሁኑ ወቅት ጌጣጌጦችና አልባሳቱ ለገበያ መቅረባቸው አዲሱ ትውልድ ማንነቱን እንዲያውቅና በባህሉ እንዲኮራ የሚያስችለው መሆኑንም ጠቅሳለች፡፡ የተለያዩ ባህላዊ ጌጣጌጦችን ለገበያ ያቀረበችው ወጣት ቃልኪዳን ሲሳይ፤ በተለይም የውጭ ሀገር ዜጎች የኢትዮጵያን ታሪክ የሚያንጸባርቁ ቅርጻ ቅርጾችንና ጌጣጌጦችን በብዛት በመሸጥ ላይ መሆኗን ተናግራለች፡፡   ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ሙሉጌታ ተካ በበኩላቸው፤ በዓሉን የሚያደምቁ የመዋቢያ ጌጦችንና አልባሳትን ቀድሞ ማዘጋጀት ዓመታዊ ተግባራቸው መሆኑን ገልጸዋል። የሚቀርቡት ውጤቶችም ወቅቱን ያማከሉና የማህበረሰቡን ፍላጎት መሠረት ያደረጉ በመሆናቸው ገበያው ንቁ መሆኑን ገልጸዋል። የጥምቀት በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አማኞች ዘንድ በየዓመቱ ጥር 11 ቀን በታላቅ ድምቀት የሚከበር ሲሆን፣ በዓሉ በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም (UNESCO) በማይዳሰስ የዓለም ቅርስነት መመዝገቡ ይታወሳል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ውጤታማ የሀብት አስተዳደርና አጠቃቀም የመንግሥት የልማት ድርጅቶችን ገቢ በከፍተኛ ሁኔታ እያሳደገው ይገኛል
Jan 17, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ጥር 9/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ሥር የሚተዳደሩ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ውጤታማ የሀብት አስተዳደርና አጠቃቀም በመከተላቸው ገቢያቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን የሆልዲንጉ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሀብታሙ ኃይለሚካኤል ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት የሀገሪቱን ቁልፍ የመንግሥትና ሌሎች የፋይናንስ ተቋማትን ያሰባሰበው “የፋይናንስ እመርታ በኢትዮጵያ” ኮንፈረንስ ተካሂዷል። በመድረኩም በ2014 የተቋቋመው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ 41 የመንግስት የልማት ድርጅቶችን ወደ አንድ በመሰብሰብ ሃብት የማወቅ፣ተበታትኖ የቆየውን ሃብት በተደራጀ መንገድ የማስተዳደር ስራ ተግባራዊ እየሆነ እንደሚገኝ ተገልጿል። በኢትዮጵያ ኢንቨትመንት ሆልዲንግስ ስር የሚገኙ የልማት ድርጅቶች የነበረባቸውን የፋይናንስ፣ የኦዲት፣የካፒታል፣የብድር ጫና እና የኮርፖሬት አስተዳደር ችግር በመቅረፍ ዘመናዊ የባለቤትነት፣ የአስተዳደር ስርዓት እና ዓለም አቀፍ የኮርፖሬት አስተዳደር ስርዓት ተዘርግቶላቸዋል። በተጨማሪም ዘመናዊ የኦዲት ስርዓት እንዲከተሉ የተደረገ ሲሆን ይህም ተቋማቱ ከኪሳራ ወጥተው ወደ ትርፋማነት እንዲሸጋገሩ ማስቻሉ ተገልጿል። ከሀገራዊ ለውጡ በፊት አብዛኞቹ የመንግስት የልማት ድርጅቶች የኢኮኖሚ ስብራት አጋጥሟቸው የነበረ ሲሆን በሆልዲንጉ ስር መተዳደር ከጀመሩ በኋላ ግን የአመራርና አስተዳደር ለውጦችን በማድረግ ወደ ትርፋማነት መሸጋገር ችለዋል። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሀብታሙ ኃይለሚካኤል በተቋሙ ሥር ያሉ ኩባንያዎችን ትርፋማነትና የሥራ ውጤታማነት ለማረጋገጥ በትኩረት ሲሰራ እንደነበር አስታውሰዋል። በዚህም ተቋማቱ ውጤታማ የሃብት አስተዳደርና አጠቃቀም በመከተል ከጊዜ ወደ ጊዜ ገቢያቸው እያደገ መምጣቱን ገልፀዋል። በዚህም በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ስር ከሚተዳደሩ ተቋማት በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት ከ1 ነጥብ 3 ትሪሊየን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን አስታውቀዋል። ገቢው ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ51 በመቶ ጭማሪ እንዳለው ጠቅሰዋል። በሆልዲንጉ ሥር የሚተዳደሩ የልማት ድርጅቶች እንደየሃብት መጠናቸው ገቢ ማስገባታቸውንም ገልጸው፥ለተገኘው ገቢ በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ ያሉ ተቋማት ከፍተኛ ድርሻ እንዳላቸው ገልፀዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ኢትዮ-ቴሌኮም፣ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ የኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ እንዲሁም የኢትዮጵያ ነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ከተገኘው ገቢ 80 በመቶውን እንደሚሸፍኑ አብራርተዋል። በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ሥር የሚተዳደሩ የልማት ድርጅቶች ከአጠቃላይ ሀገራዊ ምርት ውስጥ የ12 በመቶ ድርሻ ያላቸው ሲሆን ከፍተኛ ታክስ ከፋዮችም ናቸው። ድርጅቶቹ በ2017 በጀት ዓመት ከ228 ቢሊዮን ብር በላይ ለመንግስት ታክስ መክፈላቸውም ታውቋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ኢትዮጵያ ለትውልድ አስፈላጊ የሆኑ ተቋማትን በመፍጠርና ያሉትን በማዘመን ጠንካራ መሠረት እየገነባች ነው
Jan 17, 2026 77
አዲስ አበባ፤ጥር 9/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ለትውልድ አስፈላጊ የሆኑ ተቋማትን በመፍጠርና ያሉትን በማዘመን የኢኮኖሚ ፍላጎትና የሕዝብ ብዛት መሸከም የሚችል ጠንካራ መሠረት እየገነባች መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "የፋይናንስ እመርታ በኢትዮጵያ" በሚል በተካሄደው ኮንፈረንስ ላይ በሰጡት ማብራሪያ፤ ተቋማትን የማደራጀት ጉዳይ መነሻው ፍላጎት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ መንግሥት ሊያሳካ የሚፈልጋቸውን ግቦች ውጤታማ ለማድረግ የተቋማት ግንባታ ዋነኛው መሣሪያ መሆኑን ጠቅሰው፤ ጥሩ ሐሳብ በተቋማት ታግዞ ወደ ተግባር ካልተለወጠ ትርጉም አልባ ነው ብለዋል፡፡ የተቋም ግንባታ ሐሳቦች ከግለሰቦች አልፈው ለብዙኃን እንዲደርሱ የሚያስችል የለውጥ ምሰሶ መሆኑን አስረድተዋል። ውጤታማ ተቋም በሕግና በሥርዓት የሚመራ፣ ለተገልጋዮቹ የታመነ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነት ያለው እንዲሁም ለወደፊት መቀጠል የሚያስችል ጽኑ መሠረት የያዘ መሆን ይኖርበታልም ብለዋል። የኢትዮጵያን የፋይናንስ ዘርፍ ለመለወጥ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ አጀንዳ ሲቀረጽ ነባር ተቋማትን የማዘመን ተግባር መከናወኑን አመልክተው፤ ሌሎችን ደግሞ አዲስ በማዋቀር ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን ገልጸዋል። ከዚህ ቀደም እንደ ኢትዮጵያ ያለ ትልቅ ኢኮኖሚ ያላት ሀገር የካፒታል ገበያ እንዳልነበራት በማሳያነት የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሁን ላይ አዳዲስ አሠራሮችና አመራሮች ይዘው የመጡ ተቋማት በርካታ ለውጦችን እያስመዘገቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ እየዘመነች ባለችበት ሂደት ውስጥ መሰል ተቋማት ካልተገነቡ፣ ሐሳቦችን ተሻግሮ ለትውልድ ማድረስና ውጤት ማምጣት እንደማይቻልም አስገንዝበዋል። ያሉትን ተቋማት ማዘመንና የጎደሉትን መሙላት ዘመኑን በሚዋጅ አግባብ መሥራት ሕልም ካለው ሀገርና ኩባንያ የሚጠበቅ ተግባር መሆኑን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ለትውልድ አስፈላጊ የሆኑ ተቋማትን በመፍጠርና ያሉትን በማዘመን፣ የሀገሪቷን የኢኮኖሚ ፍላጎትና የሕዝብ ብዛት መሸከም የሚችል ጠንካራ መሠረት እየገነባች መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡  
የሀገርን ብልጽግና በማረጋገጥ ሂደት የኢንቨስትመንት ተዋናዮች ተገቢውን ሚና እንዲጫወቱ አስቻይ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jan 16, 2026 108
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018(ኢዜአ)፦ የሀገርን ብልጽግና በማረጋገጥ ሂደት የኢንቨስትመንት ተዋናዮች ተገቢውን ሚና እንዲጫወቱ አስቻይ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) "የፋይናንስ እመርታ በኢትዮጵያ" ኮንFረንስ ላይ በሰጡት ማብራሪያ በመደመር ዕሳቤ መሰረት የመንግሥትና የግሉ ዘርፍ ሚናቸው ተለክቶና ታውቆ በዚያው ልክ መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል ብለዋል፡፡ የግሉን ዘርፍ የሚያቀጭጭ እንቅስቃሴ መከተል አዳዲስ ፈጠራዎችን ያጠፋል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የፈጠራ መቀዛቀዝ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለሀገር ዕድገት ትልቅ እንቅፋት እንደሆነም አስገንዝበዋል። በመሆኑም መንግሥት የግሉ ዘርፍና አዳዲስ ሥራ ፈጣሪዎች(ስታርታፖች) እንዲጠናከሩ አመርቂ ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው፤ እንደ አፈር ማዳበሪያና ኢነርጂ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች መልክ መያዛቸው ለሀገር ብሔራዊ ጥቅም መከበር ጉልህ ሚና እንደሚጫወቱ ጠቁመዋል። የአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ ልማት ለግሉ ዘርፍ ኢንቨስትመንት የፈጠረውን ዕድል በማሳያነት ጠቅሰው፤ በልማቱ ግራና ቀኝ ባሉ እንደ ሞል፣ ሬስቶራንትና ሌሎችም ንግዶች አማካኝነት 1 ነጥብ 3 ትሪሊየን ብር ገደማ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ በመንግሥትና በግሉ ዘርፍ መካከል ያለውን ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ እየተሠራ መሆኑን ገልጸው፤ የመንግሥት የልማት ድርጅቶችም ትልቅ እመርታ እንዲያመጡ እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። ለዚህም እንደ ኢትዮ ቴሌኮምና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ያሉ ተቋማት እያስመዘገቡት ያለው ስኬት ተጠቃሽ መሆኑን አመልክተዋል። ዳያስፖራው በሀገሩ የልማት ጉዳይ ላይ ግንባር ቀደም ተሳታፊ እንዲሆን መንግሥት የጀመረውን የማበረታቻ ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም