ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ስኬታማ አቅም እየተገነባ ነው
Jun 2, 2026 325
አዲስ አበባ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ስኬታማ አቅም እየተገነባ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በፋይናንስ አቅርቦት የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማጠናከር የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። በሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ልማት ማበረታቻ የፋይናንስ አቅርቦት የትብብር ስምምነቱን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) ፈርመውታል።   የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ የዜጎቿን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጥ የተቃና ጉዞ ላይ ናት ብለዋል። የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልፅግና ለማረጋገጥም የወጣቱን ዕምቅ የፈጠራ ሃሳብና አቅም ወደ ተግባር የሚለውጥ ውጤታማ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የተቋማት ትብብርም ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትን ያረጋገጠች ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመገንባት ጉልህ ሚና እንደሚጫወት አንስተዋል። የተቋማቱ የትብብር ስምምነትም የሥራ ፈጣሪ ወጣቶችን የፈጠራ ክህሎት የሚያዳብር የፋይናንስ አቅርቦት በማመቻቸት የነገ ተስፋቸውን ምቹ ምኅዳር የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል።   ለአብነትም ኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ የአምራችነት ባህልን የሚገነባ አስቻይ ሁኔታ እየፈጠረች መሆኗን እንደሚያሳይ ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ስምምነቱ በተለያዩ ክልሎች በግብርና ዘርፍ ላይ የተሰማሩ ወጣቶችን የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት የሚያሳድግ ነው ብለዋል። የተቋማቱ ትብብር ስምምነትም የሴቶችና ወጣቶችን የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት አቅም በማሳደግ ከፍተኛ የወለድ መጠን ቅናሽ የተደረገበት መሆኑን ገልጸዋል።   በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የግብርና ኢንተርፕራይዞች ልማት ለሥራ ዕድል ፈጠራ ፕሮጀክት አስተባባሪ አሽቅ በድሩ፤ ፕሮጀክቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚተገበርና የዜጎችን የግብርና ምርታማነት የሚያሻሽል የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት የሚያስገኝ ነው ብለዋል።
የምርጫ ንቁ ተሳትፏችንን በልማት ለመድገም ተዘጋጅተናል- የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዎች 
Jun 2, 2026 189
ሃዋሳ ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በምርጫ ወቅት ያሳዩትን ንቁ ተሳትፎ በልማት ለመድገም መዘጋጀታቸውን የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ በከተማዋ የተለያዩ ምርጫ ጣቢያዎች ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት ተለጥፎ ለህዝብ ይፋ የተደረገ ሲሆን ህብረተሰቡም ውጤቶቹን እየተመለከተ ነው። ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቶችን ሲመለከቱ ኢዜአ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች በምርጫ ወቅት ያሳዩትን ንቁ ተሳትፎ በቀጣይ በልማት ሥራ እንደሚደግሙ ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል በከተማው የለኩ ቀበሌ ነዋሪው አቶ ታከለ ሱንደዶ እና የዳቶ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ቶማስ ፈልታሞ፤ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ላይ በንቃት መሳተፋቸው እንደሚያኮራቸው ገልጸዋል። አቶ ቶማስ ጨሬ እና አቶ ከበደ ዮናስ በበኩላቸው፤ ህዝብ የስልጣን ባለቤት መሆኑን ባረጋገጠበት ጠቅላላ ምርጫ ያሳዩትን ተሳትፎ በልማት እንደሚደግሙ አረጋግጠዋል። በሃዋሳ ምርጫ ክልል በ08 ምርጫ ጣቢያዎች ትናንት ድምጽ የተሰጠ ሲሆን የድምጽ ቆጠራ ተጠናቆ የተለጠፉ ጊዜያዊ ውጤቶችን ህዝቡ እየተመለከተ ነው፡፡
የሻሸመኔ ከተማ ነዋሪዎች በጠቅላላ ምርጫው ያሳዩትን ተሳትፎ በማስቀጠል ልማትን ለማፋጠን በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እንደሚወጡ ገለጹ
Jun 2, 2026 150
ሻሸመኔ ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በጠቅላላ ምርጫው ያሳዩትን ተሳትፎ በማስቀጠል ልማትን ለማፋጠን በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እንደሚወጡ የምዕራብ አርሲ ዞን የሻሸመኔ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። ነዋሪዎቹ ሂደቱን አስመልክተው ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ‎በህዝብ ድምጽ አሸናፊ ሆኖ ከሚመሰረተው መንግስት ጋር በመሆን ልማትን ለማስቀጠል መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። በምርጫው የታየው የሕዝብ ንቁ ተሳትፎን በማጎልበት ልማትን ለማጠናከር በሚደረገው ሂደት የድርሻቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውንም አክለዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡ የከተማዋ ነዋሪዎች መካከል የምዕራብ አርሲ ዞን አባ ገዳዎች ሰብሳቢ አባ ገዳ ነጌሶ ገመቹ፤ በጠቅላላ ምርጫው የታየውን የህዝቡን ጠንካራ ተሳትፎ በማስቀጠል ዴሞክራሲን ለማጎልበትና ልማትን ለማፋጠን በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል። የከተማው ነዋሪ ወይዘሮ ቀበኔ ደሶ፤ በጠቅላላ ምርጫው ህዝቡ ያሳየው ተሳትፎ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሰለጠነ ፖለቲካ ያለውን ዝግጁነትና መንግስት በህዝብ ይሁንታ ብቻ መመስረት እንዳለበት ያለውን ጽኑ ፍላጎት ያሳያል ብለዋል። ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ መሠረት ገብረማርያም በበኩላቸው፤ በድምጽ መስጠት ወቅት ያሳየነውን ንቁ ተሳትፎ ቀጣይ ልማትን በማፋጠን እንደግመዋለን ብለዋል።
በግብርና እና ሌሎች ዘርፎች የተሰማሩ ሴቶችና ወጣቶችን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ 
Jun 2, 2026 218
አዲስ አበባ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በግብርና እና ሌሎችም ዘርፎች የተሰማሩ ሴቶችና ወጣቶችን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ገለጹ፡፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በክህሎት ልማት፣ በሥራ ፈጠራ ማበረታቻ እና በፋይናንስ አቅርቦት ዙሪያ ያላቸውን የጋራ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) ፈርመውታል።   በመርሐ ግብሩ ላይ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል እንደገለጹት፤ የወጣቶችን ፍላጎት የተገነዘበ አገር የለውጥ ጉዞው የተቃና ይሆናል። የኢትዮጵን ሁለንተናዊ እድገትና የብልጽግና ጉዞ ስኬታማ ለማድረግ የወጣቱን እምቅ አቅምና የፈጠራ ሐሳቦች ማዕከል ያደረጉ ውጤታማ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዚህም የተቋማት በቅንጅት መሥራት ጠንካራ አገር ከመገንባት አኳያ ጉልህ ሚና እንደሚጫወትም አብራርተዋል። የሁለቱ ተቋማት ስምምነትም ለወጣቶችና ለሥራ ፈጣሪዎች የፋይናንስ አቅርቦትን በዘላቂነት በማቅርብ፣ የነገ ተስፋቸውን ለማለምለም ምቹ ምኅዳር የሚፈጥር መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ በተለይም የወጣቶችን በክህሎት የታገዙ የፈጠራ ሐሳቦች በፍጥነት ወደ ተግባርና ወደ አምራችነት እንዲቀየሩ ትልቅ ድልድይ እንደሚሆን ተናግረዋል።   በተለያዩ አካባቢዎች ለሚገኙ ወጣቶች አነስተኛ መጠን ያለው ብድር እና የግብዓት አቅርቦት መስጠትን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ስምምነቱ በተለያዩ ክልሎች በግብርና ዘርፍ ላይ ተሰማርተው ለሚገኙ ወጣቶች የገንዘብና የግብዓት አቅርቦት ማድረግን ያለመ መሆኑን ጠቅሰዋል። ይህንንም ተፈጻሚ ለማድረግ የፋይናንስ ተቋማቱ ቀደም ሲል ያቀርቡበት ከነበረው የወለድ መጠን ላይ ከፍተኛ ቅናሽ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል።
በጠቅላላ ምርጫው የታየው የህዝብ ተሳትፎ የልማት መነሳሳትን የሚያጠናክር ነው -የአዳማ ከተማ ነዋሪዎች
Jun 2, 2026 93
አዳማ ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የታየው የህዝብ ተሳትፎ የልማት መነሳሳትን እንደሚያጠናክር የአዳማ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። አስተያየት ሰጪዎቹ እንደተናገሩት፤ በምርጫው የታየው ተሳትፎ ለልማት እና ለእድገት በጎ አስተዋጽኦ ያለው ነው። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ሲስተር ዓለም ጀማል እንዳሉት፤ በጠቅላላ ምርጫው የታየው የህዝብ ተሳትፎ በትብብር እና በህብረት ሀገራችንን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ማሻገር እንደሚቻል ያሳየ ነው። በአዳማ ከተማ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ስራዎች እንዲቀጥሉ የበኩላቸውን እንደሚወጡም ገልጸዋል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ንጉሴ ኦብሴ፤ ህዝቡ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በሌሊት ብርድና በረጃጅም ሰልፎች ሳይበገር ያሳየው ጽናትና ቁርጠኝነት፣ ለልማት ያለውን መነሳሳት የሚያጠናክር ነው ብለዋል። ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎች እንዲቀጥሉ የሚጠበቅብኝን እወጣለሁ ብለዋል። አቶ ጌታቸው ወርቅነህ በበኩላቸው በምርጫው የታየው የህዝብ ተሳትፎ ህዝቡ ለሰላምና ለልማት ያለውን ተነሳሽነት በግልጽ ያሳየ መሆኑን ተናግረዋል። ወደ ፊትም አንድነታችንን በማጠናከር በልማት ስራዎች ላይ መረባረብ አለብን ብለዋል።
በምርጫው ላይ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በቀጣይ በጋራ ሀገር ለመገንባት ማዋል አለብን- የጅማ ከተማ ነዋሪዎች
Jun 2, 2026 213
ጅማ ፤ግንቦት 25/2018(ኢዜአ)፡- በምርጫው ላይ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በቀጣይ በጋራ ሀገር ለመገንባት ማዋል አለብን ሲሉ የጅማ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። በጅማ ከተማ ቆጠራ በተጠናቀቀባቸው የምርጫ ጣቢያዎች ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቶች እየተለጠፉ ሲሆን፣ ሕዝቡም እየተመለከተ ይገኛል። በጅማ ከተማ ባሉት 117 የምርጫ ጣቢያዎች ነዋሪዎች ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ ድምፃቸውን ሲሰጡ መዋላቸውን የጅማ ከተማ የምርጫ ክልል መግለጹ ይታወቃል። በከተማዋ ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት ሲመለከቱ ኢዜአ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች፤ አጠቃላይ በምርጫ ሂደቱ በትናንትናው እለት ደግሞ ድምፅ ለመስጠት ከማለዳ እስከ ምሽት የነቃ ተሳትፎ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም በምርጫው ላይ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በቀጣይ በጋራ ሀገር ለመገንባት ማዋል አለብን ሲሉ አስተያየት ሰጭዎቹ ተናግረዋል። ትላንት ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ድምጻቸውን ሰጥተው፣ በማለዳ ውጤት ለማየት በምርጫ ጣቢያ የተገኙት አቶ አወል አብዱረህማን፤ ሀገርን መውደድ ከሚገለጽባቸው መንገዶች አንዱ በምርጫ መሳተፍ ነው ይላሉ። ሰላማዊ ምርጫ ተካሂዶ መጠናቀቁ የኢትዮጵያና የሕዝቦቿ ትልቅ ስኬት መሆኑን ገልጸው፤ በምርጫ ያሳየነውን ተሳትፎ በሌሎች የልማት ሥራዎችም መድገም አለብን ብለዋል። ከዚህም ባለፈ የምርጫ ውጤትን በፀጋ በመቀበል የዴሞክራሲ መሠረትን ማፅናትና የሀገርን ልማት ማፋጠን ይገባል ሲሉም ገልጸዋል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ አቶ በሽር አህመድ በበኩላቸው፣ በምርጫው የነቃ ተሳትፎ አድርገው መምረጣቸውን ገልጸው፤ በቀጣይም ሀገር በምትፈልገው መስክ ሁሉ የነቃ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ቀደም ሲል በተካሄዱ ምርጫዎች ላይ መሳተፋቸውን ያስታወሱት አቶ በሽር፤ ይህ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በርካታ ዜጎች የተሳተፉበትና ሰላማዊ መሆኑ በእጅጉ እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል። በመሆኑም በምርጫው የተሳተፉ አካላት ሁሉ ውጤቱን አምኖ በመቀበል የኢትዮጵያን ዕድገትና ሰላም ሊያስቀጥሉ እንደሚገባ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። በምርጫው ድምጿን በመስጠቷ ትልቅ ደስታ እንደተሰማት የገለጸችው ወይዘሮ ዘቢባ ጀማል በበኩሏ፣ ውጤቱን ለማየት በማለዳው በጊንጅ ጉድሩ ቀበሌ ገጠር ቴክኖሎጂ ምርጫ ጣቢያ መገኘቷን ተናግራለች። በቀጣይም በምርጫው ላይ ያደረጉትን ተሳትፎ ሀገር በምትፈልገው የልማት ሥራዎች ላይ ለመድገም ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል። በጅማ ከተማ የኢዜአ ሪፖርተር ተዘዋውሮ በተመለከታቸው በጊንጅ ጉድሩ ቀበሌ ገጠር ቴክኖሎጂ ምርጫ ጣቢያ፣ በውኃ ፍሳሽ ምርጫ ጣቢያ እና በሌሎችም ጣቢያዎች የምርጫ ውጤቶች በአሁኑ ሰዓት እየተለጠፉ ይገኛሉ።  
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከእንጦጦ እስከ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ያለውን የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ስራ አስጀመሩ
Jun 2, 2026 302
አዲስ አበባ፤ግንቦት 25/2018(ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከእንጦጦ እስከ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ያለውን መልሶ ማልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት በይፋ ስራ አስጀምረዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ከ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ማግስት፣ዛሬ ጠዋት ከእንጦጦ እስከ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ያለውን የመልሶ ማልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት በይፋ ስራ አስጀምረናል ብለዋል።   ‎‎ይህ ትልቅ ተነሳሽነት፤የተራቆቱ አካባቢዎችን በዘመናዊ የአፈር ጥበቃ እና በወንዝ ማጣራት ወደ አረንጓዴ ስፍራዎች በመቀየር፣ የፍራፍሬ ፓርኮችን ከእግር ጉዞ እና ከብስክሌት መንገዶች ጋር በማቀናጀት መዲናችንን አድሷል ነው ያሉት።   ፕሮጀክቱ ‎በአጠቃላይ 22.25 ኪሎ ሜትር የወንዝ ዳርቻ ልማትን የሚሸፍን መሆኑን ገልጸው፥ይህ የማይቆራረጥ የልማት ስራችን ህያው ምስክር ከመሆኑም በላይ የሃገራዊ ዕድገታችን፣ የአካባቢ ጥበቃ እና የከተማ እድሳት በተግባር የታየበት ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ከተሞች የመሬት ይዞታ ካዳስተር ምዝገባ ሥርዓት የገቢ አቅማቸውን በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው
May 29, 2026 2096
አዲስ አበባ፤ግንቦት 21/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ከተሞች የመሬት ይዞታ ካዳስተር ምዝገባ ሥርዓት የከተሞችን የገቢ አቅም በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ፈንታ ደጀን ገለጹ። ከተሞች የገቢ አቅማቸውን በመጠቀም ብድር ማግኘት የሚችሉበትን ሥርዓት ለመዘርጋት እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ለኢዜአ እንዳሉት፤ ከተሞች ለአጠቃላይ ሀገራዊ ምርት ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው ናቸው። የኢትዮጵያ ከተሞች እስከ 58 በመቶ ለአጠቃላይ ሀገራዊ የምርት ድርሻ እያበረከቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ በኮሪደር፣ወንዝ ዳርቻና ዲጂታላይዜሽን የተከናወኑ ስኬታማ የልማት ተግባራት ስሉጥ ከተሞችን በመፍጠር ከፍተኛ ጠቀሜታ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊ የከተሜነት ምኅዳር የመፍጠር ሥራም ዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ የመንግሥት አገልግሎት የሚያገኙበት አስቻይ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን አንሰተዋል። የከተሞች ማዘጋጃ ቤታዊና የተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ ወደ ዲጂታል ሥርዓት መሸጋገሩም ፈጣንና ቀልጣፋ ምኅዳር መፍጠሩን አስረድተዋል። በተለይም በአንድ ማዕከል አገልግሎት ዜጎች የመንግሥት አገልግሎቶችን በተማከለ ሥርዓት በጥራትና ፍጥነት የሚያገኙበት ዕድል እንደፈጠረ ተናግረዋል። የከተሞችን የመሬት ይዞታ በፍትሐዊነት ለማስተዳደርም ምዝገባ እየተካሄደ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ 6 ነጥብ 6 ሚሊየን ፐርስል የከተማ መሬት ውስጥ 33 በመቶው ባለፉት ሶስት ዓመታት መመዝገቡን ጠቅሰው፤ በካዳስተር ስርዓት መሬትን የማስተዳደር ስራ በስፋት እየተሰራ ነው ብለዋል። ለአብነትም የአዳማ ከተማን ጨምሮ ሌሎች ከተሞች የመሬት ምዝገባ ማጠናቀቃቸው አብራርተዋል። የከተሞችን ሃብትና ገቢ የማመንጨት አቅም ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራትም ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ እንደሚገኙ አብራርተዋል። በዚህም አሁን ላይ የከተሞች ገቢ ከአራት ዓመታት በፊት ከነበረበት 10 ቢሊዮን ብር ወደ 80 ቢሊየን ብር ማድረስ እንደተቻለ ገልጸዋል። ይህም የከተሞችን ገቢ የመሰብሰብ አቅም በማሳደግ በሚያመነጩት ገቢ መጠን በመጠቀም ብድር የሚያገኙበት ሥርዓት እየተዘረጋ መሆኑን ተናግረዋል።
የአቮካዶን ምርታማነት በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታ ለማሻሻል እየተሰራ ነው
May 29, 2026 1328
አዲስ አበባ፤ግንቦት 21/2018(ኢዜአ)፦ የአቮካዶን ምርታማነት በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታ ለማሻሻል እየተሰራ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ደሳለኝ ተሻለ ገለጹ፡፡ በግብርና ሚኒስቴር አዘጋጅነት በብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ዙሪያ የዘርፉን ባለድርሻ አካላት ያሳተፈ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ደሳለኝ ተሻለ እንዳሉት፤ የአቮካዶ ምርት በአገር ደረጃ ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው የግብርና ምርት ኢኒሼቲቮች ውስጥ አንዱ ሲሆን፣ ምርትና ምርታማነቱን በማሳደግ ረገድ ሰፊ ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። ይህ ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም በአገሪቱ እያደገ የመጣውን የፍራፍሬ ፍላጎት ለማሟላትና የኢትዮጵያን የኤክስፖርት አቅምን ለማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው ጠቁመዋል። የአቮካዶ ምርት ለተመጣጠነ ምግብ አቅርቦት፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ እንዲሁም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎች እንዳሉትም አብራርተዋል። ሚኒስቴሩ አገር አቀፍ የአቮካዶ ልማትን ይበልጥ ለማስፋፋት፣ ምርታማነትን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገርና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ የዘርፉን ተዋናዮች፣ አምራቾችና ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ መልኩ በቅንጅት እየሠራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም መሠረት ከፍተኛ ምርት የሚሰጡና የተለያዩ በሽታዎችን የሚቋቋሙ ተመራጭ የአቮካዶ ዝርያዎች ለአርሶ አደሮች ተሰራጭተው ከፍተኛ ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። አነስተኛ አምራች አርሶ አደሮችን በክላስተር በማደራጀት፣ ዘመናዊ የኩሬ አጠቃቀምና የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂ ስልጠናዎችን በመስጠት የምርት ጥራትን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ማድረግ የሚያስችል አሠራር እየተዘረጋ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህም አርሶ አደሩን በቀጥታ ከዓለም አቀፍ ገበያ ጋር ለማስተሳሰር ትልቅ ሚና ይጫወታል ብለዋል። ይህ ብሔራዊ ፕሮግራም የአርሶ አደሩን የኑሮ ዘይቤና ገቢ ከመቀየር ባለፈ፣ በግብርናው ዘርፍ የሚገኘውን የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ገቢ በከፍተኛ መጠን ለማሳደግ የተቀረጸ ስትራቴጂካዊ እርምጃ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
በደቡብ ኦሞ ዞን በዘንድሮው የበልግ እርሻ ለገበያ ተኮር ሰብሎች ትኩረት ተሰጥቷል
May 29, 2026 967
ጂንካ፤ግንቦት 21/2018(ኢዜአ):- በደቡብ ኦሞ ዞን በዘንድሮ የበልግ እርሻ ለገበያ ተኮር ሰብሎች ትኩረት በመስጠት መሰራቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ በዞኑ በዘንድሮ የበልግ እርሻ 108 ሺህ ሄክታር መሬት መልማቱን ገልጸዋል።   አጠቃላይ ከለማው መሬት ወደ 4 ሚሊዮን የሚጠጋ ምርት ለማግኘት እንደታቀደም ጠቅሰዋል። በዘንድሮ የበልግ እርሻ ለገበያ ተኮር እና የኢንዱስትሪ ግብዓት ለሚሆኑ ስንዴ፣ ሰሊጥ፣ ካሳቫ እና ማሾ ሰብሎች ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። ቀደም ሲል አርሶና አርብቶ አደሩ ውስን ሰብሎችን ብቻ በማልማት ለገበያ የሚያቀርብበትን ሁኔታ በመቀየር ገበያ ተኮር የሆነ አመራረት በመከተል በኩታ ገጠም በስፋት የሚያለሙበት ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። ከዚህም ባሻገር አርሶና አርብቶ አደሩ በአካባቢው ያልተለመዱ እንደ ሩዝ እና ካሳቫ ምርቶችን ማምረት መጀመራቸውን አንስተው፥ በዚህም የገቢ አቅማቸው እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል።   በዞኑ ሳላማጎ ወረዳ ገሮ ቀበሌ በካሳቫ ምርት የተሰማሩት አርሶ አደር አለሙ ላስታ፥ በዘንድሮ የበልግ አዝመራ 17 ሄክታር መሬት ላይ ካሳቫ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል ። መንግስት የእርሻ መሬት እና የእርሻ ትራክተር በማቅረብ እገዛ እያደረገላቸው መሆኑን ገልፀው፥ የግብርና ባለሙያዎችም ገበያ ተኮር የሆኑ ሰብሎችን እንዲያለሙ ሙያዊ ድጋፍ እያደረጉላቸው መሆኑን ገልጸዋል። ካሳቫ በአንድ ሄክታር እስከ 300 ኩንታል ምርት የሚያስገኝ እና ቶሎ የሚደርስ ሰብል መሆኑ ደግሞ ይበልጥ ተመራጭ አድርጎታል ነው ያሉት አርሶ አደሩ።   ሌላው የወረዳው አርሶ አደር አድማሱ ጩሉ፥ በዘንድሮ የበልግ አዝመራ በኩታ ገጠም 8 ሄክታር መሬት ላይ ሩዝ እያለሙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሩዝ ውሃ በሚተኛባቸው ረግረጋማ ቦታዎች ምርት የሚሰጥ በመሆኑ ሩዝ እያለሙ መሆኑን ገልጸዋል። በአካባቢው ቀደም ሲል በቆሎ እና ማሽላ በስፋት የማልማት ልምድ እንደነበር ጠቁመው፥ አሁን ላይ በመንግሥት ድጋፍ ገበያ ተኮር የሆኑ ሰብሎችን በማልማት የተሻለ ገቢ ማግኘት መጀመራቸውን ገልጸዋል።
የመስኖ ግድቦች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገውን ጉዞ እያፋጠኑ ነው
May 28, 2026 1438
ነገሌ ቦረና፣ግንቦት 20/2018 (ኢዜአ)፦በምሥራቅ ቦረና ዞን አነስተኛና መካከለኛ የመስኖ ግድቦች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገውን ጉዞ እያፋጠኑ መሆኑን የዞኑ መስኖና አርብቶ አደር ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የምሥራቅ ቦረና ዞን አብዛኛው ነዋሪ ሕይወትና መተዳደሪያው አርብቶ አደርነትና ከአነስተኛ የእርሻ ሥራ ጋር የተያያዘ ነው። አካባቢው በተደጋጋሚ ጊዜ በሚከሰት ድርቅና በተለዋዋጭ የአየር ንብረት መዛባት ምክንያት ከፍተኛ የሆነ የውኃ እጥረት ሲያጋጥመው ቆይቷል። ይህንን ለመፍታት ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ትኩረት የተሰጠው አነስተኛና መካከለኛ የመስኖ መሠረተ ልማቶችን ማስፋፋት ላይ ነው። የመስኖ ግድቦቹ መገንባት ማኅበረሰቡ መደበኛውን የዝናብ ወቅትን ብቻ ከመጠበቅ ወጥቶ፣ ያለውን የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር ውኃ በአግባቡ በመጠቀም በዓመት ሁለትና ሦስት ጊዜ እንዲያመርት ዕድል ፈጥሯል። የዞኑ መስኖና አርብቶ አደር ጽሕፈት ቤት እንዳስታወቀው፤በዞኑ ቆላማ ወረዳዎች የተገነቡ ሁለት የመስኖ መሠረተ ልማቶች እየሰጡ ባለው አገልግሎት ዘርፈ ብዙ ጥቅም እያስገኙ ነው። በጽሕፈት ቤቱ የዲዛይንና ቁጥጥር ቡድን መሪ ኢንጂነር ተስፋሁነኝ ዳንኤል እንደገለጹት፤ ፕሮጀክቶቹ በተለይም ከተረጂነት ወደ ምርታማነት በሚደረገው ሽግግር ውስጥ ትልቅ እገዛ እያደረጉ ነው። በተለይም በዞኑ በሊበንና በጎሮዶላ ወረዳዎች የተገነቡት ግድቦቹ ነዋሪውን ወደ መስኖ ልማት ማስገባት ያስቻሉ ሲሆን ለምርታማነት ዕድገትም አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው ብለዋል። እነዚህ የመስኖ ፕሮጀክቶች ከ8 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የዝናብ ውኃ የማጠራቀም አቅም እንዳላቸውም ገልጸዋል። የመስኖ ፕሮጀክቶቹ ከ465 ሄክታር በላይ መሬትን በዘመናዊ መስኖ ከማልማት ጎን ለጎን፣ የአካባቢውን የመኖና የውኃ ችግር የሚያቃልሉ መሆናቸውንም አስረድተዋል። በተጨማሪም ግድቦቹ ለአሳ ሀብት ልማትና ለቱሪዝም መዳረሻነት አገልግሎት እንዲሰጡ ተደርገው የተገነቡ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ለአብነትም በዞኑ ድቤ አዳማ መስኖ ፕሮጀክት ግድብ ውስጥ እስካሁን ከ10 ሺህ በላይ የአሳ ጫጩቶች መለቀቃቸውን ገልጸዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የዞኑ ነዋሪዎች እንዳሉት፥የመስኖ ፕሮጀክቶቹ በዘመናዊ መስኖ ልማት የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥ ያግዛቸዋል። በዞኑ ሊበን ወረዳ የሲሚንቆ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ቃሲም ገመዳ እንደገለጹት፤ አካባቢው በድርቅና በዝናብ እጥረት ሳቢያ በተደጋጋሚ የመኖና የውኃ ችግር ያጋጥመው ነበር። ቀደም ሲል መኖና ውኃ ፍለጋ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ በሚያደርጉት እንቅስቃሴ ለከፍተኛ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ሲጋለጡ መቆየታቸውንም ያስታውሳሉ። በአካባቢያቸው በተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት የበጋ ስንዴን በዘመናዊ መስኖ በማልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዲሁም የእንስሳት መኖና የውኃ ችግርን ለማቃለል እንደሚያግዝ ጠቁመው፥የበጋ ስንዴ፣ ቲማቲም፣ድንችና ሽንኩርት በመስኖ ለማልማት ተዘጋጅተዋል። ሌላው ነዋሪ አቶ ጉዮ ጃተኒ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል መደበኛ ሥራቸውን ትተው የእንስሳት መኖና የመጠጥ ውኃ ፍለጋ ሩቅ መንገድ ይጓዙ እንደነበር ያስታውሳሉ። በአካባቢያቸው የተገነቡት የመስኖ ፕሮጀክቶች ከአካባቢያቸው ሳይርቁ የበጋ ስንዴ በማምረት ችግሩን በዘላቂነት ለመቋቋም እንዳስቻላቸው ገልጸዋል።
በጂማ ከተማ የሥራ ዕድል የተመቻቸላቸው ወጣቶች ተጠቃሚነታቸው አድጓል
May 28, 2026 368
ጂማ፣ ግንቦት 20/2018 (ኢዜአ)፦ በጂማ ከተማ በተለያዩ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ወጣቶች ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ገለጹ። በከተማዋ የወጣቶችን የሥራ ዕድል ለማስፋት የግብርና፣ የቴክኖሎጂና የንግድ ሥልጠናዎችን በመስጠት፣ የመሥሪያና መሸጫ ቦታዎችን በማቅረብ እንዲሁም የገበያ ትስስር በመፍጠር ረገድ ተስፋ ሰጪ ውጤቶች እየተመዘገቡ ይገኛሉ። በከተማዋ ኢዜአ ያነጋገረው ወጣት አብዱረሂም ናስር እንደገለጸው፤ የከተማ አስተዳደሩ ባመቻቸለት የሥራ ዕድል በመጠቀም የዳቦ መጋገሪያ ማሽኖችን በጥራት አምርቶ ለገበያ እያቀረበ ይገኛል። እነዚህ ማሽኖች ከውጭ የሚገቡ የዳቦ መጋገሪያ ምርቶችን በመተካት የውጭ ምንዛሬን ከማዳናቸው ባለፈ፣ ኃይል ቆጣቢ በመሆናቸው በገበያ ላይ ተመራጭ መሆናቸውን አስረድቷል። ይህም ገቢውን ከመጨመር ባለፈ ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል እንዲፈጥር እንዳገዘው ጠቁሟል።   በተመሳሳይ ዘመናዊ ቦርሳዎችንና የቆዳ ውጤቶችን በማምረት ለገበያ እያቀረቡ ከሚገኙ ወጣቶች መካከል ደርሶልኝ ሽመልስ እና ሀብታሙ ጋዲሳ ይጠቀሳሉ። ወጣቶቹ እንደሚያስረዱት፤ የሚያመርቷቸው የቆዳ ውጤቶች በቅርጽም ሆነ በጥራት የሸማቹን ፍላጎት ያሟሉ በመሆናቸው በገበያ ላይ ተወዳዳሪ መሆን ችለዋል። ሥራቸውን ይበልጥ ለማስፋፋትም የከተማ አስተዳደሩ የብድርና የመሥሪያ ቦታ እንዳመቻቸላቸው ገልጸዋል። የጂማ ከተማ የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት መምሪያ ኃላፊ አቶ አብዱልሀሚድ ኑረዲን በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በከተማዋ ለወጣቶች የሥራ ዕድልን ለማስፋፋት በርካታ የመሥሪያና የመሸጫ ሼዶች ተገንብተዋል።   በዚህም በበጀት ዓመቱ ከ3 ሺህ በላይ በማኅበራት ለታቀፉ 20 ሺህ 160 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ፣ ዕቅዱን በማሳለጥ 28 ሺህ 500 ወጣቶችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል። የወጣቶቹን ስኬት ይበልጥ ለማገዝ የሥልጠናና የብድር አቅርቦት መመቻቸቱን የገለጹት ኃላፊው፤ በበጀት ዓመቱ እስካሁን 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር የብድር አገልግሎት መቅረቡን ጠቁመዋል። ለወጣቶቹ የሥራ ዕድልን ለማስፋፋትም ለቡና መፈልፈያ፣ ለዳቦና እንጀራ መጋገሪያ፣ ለቆዳና እንጨት ሥራዎች እንዲሁም ለሌሎችም ተኪ ምርቶች ማምረቻ የሚሆኑ ሼዶች መሰጠታቸውን አክለዋል። ወደ ሥራ የገቡት ወጣቶች ምርቶቻቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ ለሕብረተሰቡ ከማቅረብ ባለፈ፣ ተኪ ምርቶችን በማምረት የሀገርን የውጭ ምንዛሬ ማዳን መቻላቸውንም አቶ አብዱልሀሚድ ገልጸዋል።  
በአማራ ክልል በዘንድሮው መኸር እርሻ ከ876 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት በሰሊጥና አኩሪ አተር ይለማል
May 28, 2026 323
ባህርዳር ፤ ግንቦት 20/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በዘንድሮው መኸር እርሻ ከ876ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ለኢንዱስትሪና ለውጭ ገበያ የሚውል የሰሊጥና የአኩሪ አተር እንደሚለማ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ሰሊጥ ከቡና ቀጥሎ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ከሚያስገኙ የግብርና ምርቶች መካከል ተጠቃሽ ነው። አኩሪ አተርም ለምግብ ዘይት ፋብሪካዎችና ለእንስሳት መኖ ኢንዱስትሪዎች ወሳኝ ግብዓት ከመሆኑም በላይ፣ በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ያለው ተፈላጊነት እየጨመረ የመጣ ሰብል ነው። ‎ ‎በአማራ ክልል ግብርና ቢሮ የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማንደፍሮ አስላከ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለፁት ለኢንዱስትሪና ለወጪ ምርት ግብዓት የሚውሉ ሰብሎችን በጥራትና በብዛት ለማምረት ግብ ተይዞ እየተሰራ ነው። ‎ ‎በዚህም በዘንድሮው የመኸር እርሻ የአየር ንበረታቸውና ስነ ምህዳራቸው ተስማሚ በሆኑ አካባቢዎች የሰሊጥና አኩሪ አተር ሰብሎች በስፋት ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ብለዋል። በዚህም በክልሉ ከሚለማው 876ሺህ 870 ሄክታር መሬት፤ 463ሺህ 566 ሄክታር በሰሊጥ ቀሪው ደግሞ በአኩሪ አተር እንደሚለማ ተናግረዋል። ‌‎ከልማቱ ከ15 ነጥብ 3 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ጠቁመው የዘር ወቅት በመድረሱም ዘርና ማዳበሪያ እየቀረበ ነው ብለዋል።
ባሕር ዳር ለነዋሪዎቿ ምቹ ለዓለምአቀፍ ጎብኚዎች ደግሞ ተመራጭ የቱሪስት ከተማ እየሆነች ነው - ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው
May 27, 2026 1029
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ ባሕር ዳር በኮሪደር ልማት ለነዋሪዎቿ ምቹ ለዓለምአቀፍ ጎብኚዎች ደግሞ ተመራጭ የቱሪስት ከተማ እየሆነች ነው ሲሉ የባህርዳር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ። የባሕር ዳር ከተማን ውበትና ፅዳት በመጠበቅ ለነዋሪዎች ምቹ፣ ለዓለም አቀፍ ጎብኚዎች ደግሞ ተመራጭና ረጅም ጊዜ የሚቆዩባት የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ የተቀረጸው ዕቅድ በተግባር እየተተረጎመ ይገኛል። ​የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው እንደገለጹት፣ ይህንን ግብ ለማሳካት የተቋቋመው የስማርት ባህርዳር ፕሮጀክት ፅህፈት ቤት መሪነቱን በመውሰድ የኮሪደርና የጣና ዳርቻ ልማቶችን ሌሊትና ቀን በከፍተኛ ፍጥነት እያከናወነ ነው።   ​የከተማዋን ገጽታ የቀየሩ የጣና እና የዓባይ ዳርቻ ፕሮጀክቶች ​የከተማዋ ተፈጥሯዊ ሀብቶች የሆኑትን የጣና ሐይቅንና የዓባይ ወንዝን ለቱሪዝም ምቹ የማድረግ ሥራ ትኩረት ተሰጥቶታል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅት በሐይቁ ዳርቻ ላይ ዘጠኝ የሚደርሱ ቦታዎች መልማታቸውን ጨምረው አስታውቀዋል። ይህም ከተማዋ፣ ነዋሪዎችና ጎብኚዎች ከሐይቁ ጋር ያላቸውን መስተጋብር በእጅጉ አሳድጎታል ብለዋል። ከዚሁ ልማት ጋር ተያይዞም የዘንባባ ፓርክ ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑ የከተማዋን ውበት ይበልጥ እንዳደመቀው ገልጸዋል። ​የኮሪደር ልማቱ ​የከተማዋን ዋና ዋና መስመሮች እያደሰ ያለው የኮሪደር ልማት ከደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተነስቶ እስከ ዓባይ ማዶ ባለው ዋና መንገድ ላይ በከፍተኛ ፍጥነት እየተገነባ ይገኛል ብለዋል።   ይህ መሠረተ ልማት ከ5 እስከ 7 ሜትር የሚደርስ ሰፊ የእግረኛ መንገድ፣ እስከ 4 ሜትር ስፋት ያላቸው ውብ አረንጓዴ መናፈሻዎች፣ ​እስከ 3 ሜትር ስፋት ያለው የተለየ የብስክሌት መንገድ፣ የስፖርት ማዘውተሪያዎች፣ የሕዝብ ማረፊያዎችና የሕፃናት መጫወቻዎች ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። ​በተጨማሪም ከቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን እስከ ፓፒረስ ሆቴል ድረስ ያለው የእግረኛ መንገድ ግንባታ እየተፋጠነ እንደሚገኝም አንስተዋል። በከተማዋ የዓባይ ወንዝን ዳርቻን ለማልማት መታቀዱንም ነው የጠቆሙት። ​የከተማዋ የኮሪደር ልማት ዕቅድ ሲቀረጽ ጀምሮ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህን ጨምሮ የፌደራል መንግሥቱ ፕሮጀክቱን በመገምገምና አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ የላቀ የመሪነት ሚና መጫወታቸውንም አስረድተዋል። ​ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በከተማዋ ተገኝተው የልማት ሥራዎቹን መገምገማቸውንና ለቀጣይ ተግባራት አቅጣጫ ማስቀመጣቸውንም ነው ያነሱት አቶ ጎሹ እንዳላማው።   ለኮሪደር ልማቱ ስኬት የከተማዋ ነዋሪዎችና ባለሀብቶች በገንዘብና በሐሳብ እያደረጉት ያለው ተሳትፎ አይተኬ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። ከተማ አስተዳደሩ ሕዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ መሰል የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው አረጋግጠዋል።
መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 376
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ ‎የሕዝብ ጤናን እየጠበቅን፣ የነዋሪዎችን መተዳደሪያ አቅም እያጠናከርን መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ግዙፉ የቦረና የመጠጥ ውኃ አቅርቦትፕሮጀክት ለኅብረተሰቡ አስተማማኝ የንጹሕ ውኃ አቅርቦት ተደራሽ በማድረግ፣ በምሥራቅ ቦረና እና በቦረና ዞኖች የሚገኙ ነዋሪዎችን ሕይወት እየቀየረ ይገኛል ብለዋል። በብዙ ኪሎ ሜትሮች የሚቆጠሩ የቧንቧ መስመሮችን፣ ዘመናዊ የውኃ ማከፋፈያ ጣቢያዎችን እና ሰፋፊ የውኃ ማጠራቀሚያዎችን ያካተተ ዘላቂ መሠረተ ልማት እየገነባን ሲሆን ይህም ድርቅን ከመመከት የላቀ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። ‎ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት ‎የሕዝብ ጤናን እየጠበቅን፣ የነዋሪዎችን መተዳደሪያ አቅም እያጠናከርን መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን ብለዋል።
በአዳማ ከተማ በተለያዩ ዘርፎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነዋሪዎች ውጤታማ በመሆናቸው ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል ፈጥረዋል
May 27, 2026 308
አዳማ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ በአዳማ ከተማ በተለያዩ ዘርፎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነዋሪዎች ውጤታማ በመሆናቸው ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ገለጹ።   ከተጠቃሚዎቹ መካከል አቶ ጌቱ ተስፋዬ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ከተማ አስተዳደሩ በቤተሰብ ብልጽግና ተደራጅተው ራሳቸውንና ማኅበረሰቡን ተጠቃሚ እንዲያደርጉ ከፍተኛ ድጋፍ እንዳደረገላቸው ገልጸዋል። በከተማዋ ቦሌ ክፍለ ከተማ በተመቻቸላቸው የመሥሪያ ቦታ ላይ ከአምስት የቤተሰብ አባላት ጋር በመደራጀት በዚህ ዓመት ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል።   መንግሥት ባመቻቸላቸው የ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ብድር በዳቦ ማምረቻ ኢንተርፕራይዝ ተደራጅተው ምርታቸውን ለአካባቢው ማኅበረሰብ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን አስረድተዋል። አሁን ላይ ከራሳቸው አልፈው ለ10 ተጨማሪ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን አውስተዋል። ሌላኛው በዱቄት ማምረቻ ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ገዙ በዳዳ በበኩላቸው፤ መንግሥት ወደ ልማት እንዲገቡ እንዲሁም ተጠቃሚ እንዲሆኑ ትልቅ እገዛ ማድረጉን ገልጸዋል። ከተማ አስተዳደሩ የመሥሪያ ቦታ ከመስጠትና መሠረተ ልማት ከማሟላት ባለፈ፣ ከባንክ የ2 ሚሊዮን ብር ብድር እና የካፒታል ማሽን አቅርቦት እንዲያገኙ በማመቻቸት በሙሉ አቅማቸው ወደ ሥራ እንዲገቡ ድጋፍ ማድረጉን አመልክተዋል።   አቶ ገዙና የቤተሰባቸው አባላት የዱቄት ማምረቻ ማኅበር በቀን 330 ኩንታል የስንዴ ዱቄት በማምረት ለዳቦ ፋብሪካዎችና ለኅብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ ይገኛሉ ብለዋል። በዚህም ውጤታማ መሆን ከመቻላቸው ባለፈ ለስምንት ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ገልጸዋል።   የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው፤ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የቤተሰብ ብልጽግና ፓኬጅ በከተማዋ በተደራጀ መልኩ ተግባራዊ እየተደረገ ነው ብለዋል። ይህ አሠራር እያንዳንዱን ቤተሰብ ለለውጥና ለዕድገት በማነቃቃት፣ ለመበልፀግ በቁጭት እንዲነሱ ማድረጉን ጠቁመው፤ ተሳታፊዎች የጠራ ግንዛቤ ይዘው ሥራ ውስጥ እንዲገቡ እየተደረገ ይገኛል ነው ያሉት። በበጀት ዓመቱ ለቤተሰብ ብልጽግና ተሳታፊዎች የሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን የጠቀሱት ከንቲባው፤ ለዚህም አስተዳደሩ የመሥሪያና የመሸጫ ቦታዎችን እንዲሁም የብድር አቅርቦትን ለማመቻቸት እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህ ዓመት በከተማዋ በተገነቡ በርካታ ሼዶች 89ሺህ የከተማዋ ወጣቶችና ነዋሪዎች በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዘርፎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆን ችለዋል ብለዋል።
ሀዋሳ ከተማን ለነዋሪዎች ምቹ እና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጠናክሮ ይቀጥላል
May 27, 2026 261
ሀዋሳ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን ለነዋሪዎች ምቹ እና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ከከተማው ከንቲባና ከተለያዩ ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች ጋር በመሆን፤ በከተማዋ ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።   ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በምረቃው መርሃ ገብር እንዳሉት፤ የለውጡ መንግስት ለከተሞች በሰጠው ልዩ ትኩረት የከተሞችን ዕድገት የሚያፋጥኑ ዘርፈ-ብዙ የልማት ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በዚህም ሀዋሳን ለነዋሪዎቿ ምቹ፣ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት ደግሞ ተመራጭ ለማድረግ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ቀጣይነት ለማረጋገጥ ህብረተሰቡን ያሳተፈ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።   በከተማዋ የተመረቁት የልማት ፕሮጀክቶች በኮሪደር ልማት የተጀመሩ ሥራዎችን ከማጠናከር ባለፈ፤ የአገልግሎት አሰጣጥን በማሳለጥ የሕዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች የሚመልሱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የክልሉ መንግስት ሀዋሳን የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ ለቱሪዝም መስህብ ልማቶችና ለአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ማስፋፊያ ልዩ ትኩረት መስጠቱንም አንስተዋል።   የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው፤ የሀዋሳን የኮሪደር ልማትና ሁሉን አቀፍ የልማት ፕሮጀክቶች በማፋጠን ከተማዋን የቱሪዝምና የኢንዱስትሪ ማዕከል ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በከተማዋ በመደመር እሳቤ የሚከናወኑት የልማት ፕሮጀክቶች በተለይም በጥራት ላይ ማተኮራቸውን አብራርተዋል። ዛሬ ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የአዳሬ አጠቃላይ ሆስፒታል ማስፋፊያ፣ የአጠቃላይ ትምህርት ቤቶች ማስፋፊያ ግንባታ እና ሌሎች መሰረተ-ልማቶች ይገኙበታል ብለዋል። እነዚህ ፕሮጀክቶች በአጠቃላይ ከ2 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው መሆኑን ከንቲባው አስታውቀዋል።   የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዋ ሲስተር እልፍነሽ ናኡሼ፤ በሃዋሳ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች ከተማዋን አዲስ ገጽታ እያላበሷት መሆኑንና የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች አዲስ የሥራ ዕድል እየፈጠሩ እንደሚገኙ አክለዋል።   ሌላኛው የከተማው ነዋሪ አቶ ተስፋዬ አበባው፤ ዛሬ በከተማዋ የተመረቁት ፕሮጀክቶች በተለይም በጤናው ዘርፍ የነበሩትን ውስንነቶች ከመቅረፍ አንጻር ትልቅ ሚና እንደሚኖራቸው ገልጸዋል። በምረቃ መርሃ-ግብሩ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር)፣ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎችና የሕብረተሰብ ተወካዮች ተገኝተዋል።
የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የበለጠ ያነቃቃል
May 27, 2026 163
ነገሌ ቦረና፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የበለጠ የሚያነቃቃ መሆኑን የዞኑ ነዋሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የሀገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውንና አዲሱን የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያን ዛሬ በይፋ መርቀዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው እንደ ቦይንግ 737 ማክስ ያሉ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን የማስተናገድ አቅም ያለው ይህ ዘመናዊ አውሮፕላን ማረፊያ፤ የአካባቢውን እንዲሁም ድንበር ተሻጋሪ የንግድ ልውውጥን እና ቱሪዝምን የማሳደግ ራዕይን ሰንቆ በሳምንት ሦስት በረራዎችን የሚያስተናግድ ነው ብለዋል። በምስራቅ ቦረና ዞን የተገነባው ይኸው የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑ፣ ምቹ፣ ፈጣንና ቀልጣፋ የትራንስፖርት አገልግሎት ለማግኘት እንደሚያስችላቸው የዞኑ ነዋሪዎች ገልጸዋል። የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪው እንዳለ መገርሳ እንደገለጹት፤ የአውሮፕላን ማረፊያው በየብስ ትራንስፖርት ረጅም ጉዞ ምክንያት ይደርስ የነበረውን እንግልትና ችግር በእጅጉ ያቃልላል። ዞኑ በእንስሳት ሀብትና የስንዴ ምርት የሚታወቅ ቢሆንም፣ ምርቱን ለማጓጓዝ የትራንስፖርት እጥረት ያጋጥም እንደነበር አስታውሰው፣ አውሮፕላን ማረፊያው የምርት ዝውውርን የበለጠ ያቀላጥፋል ብለዋል። ይህም ለአካባቢው ኢኮኖሚና ቱሪዝም እድገት ካለው አስተዋጽኦ ባሻገር የመንገደኞችን ጉዞ ምቹ፣ ቀላልና ፈጣን እንደሚያደርገው ገልጸዋል። በዘመናዊ ትራንስፖርት ለመጠቀም የነበራቸው ምኞት በመሳካቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል። ሌላው የነገሌ ቦረና ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ ፈንታ ገረመው በበኩላቸው፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ስራ መጀመር የዞኑን ልማትና እድገት እንደሚያፋጥን ገልጸዋል። በተለይም የነገሌ ቦረና ከተማን የንግድና የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አብራርተዋል። ሌላው በዞኑ ሊበን ወረዳ ነዋሪ ቢሉ ቢርቢርሳ የአውሮፕላን ማረፊያው መንግስት ለአርብቶ አደሩ አካባቢ የሰጠውን ትኩረትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት በተግባር ያረጋገጠ መሆኑን አንስተዋል። ለአካባቢው ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል እንደሚፈጥር፣ የግብርና ምርቶችና ግብአቶች በወቅቱና በፈጣን ሁኔታ እንዲጓጓዙ እንደሚረዳና ባለሀብቶች እንዲሁም ተጓዦች ወደ ዞኑ በቀላሉ እንዲመጡ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ጠቅሰዋል። በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ የሀገር ሽማግሌዎች፣ አባገዳዎች፣ የፌደራል፣ የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በርካታ ቁጥር ያለው የዞኑ ህዝብ ተገኝቷል።
የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ መመረቅ ፍትሐዊና ሚዛናዊ የመሠረተ ልማት ዝርጋታን የሚያረጋግጥ ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 221
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፦ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ መመረቅ ፍትሐዊና ሚዛናዊ የመሠረተ ልማት ዝርጋታን የሚያረጋግጥ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን የገለጹት የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የሀገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውን ይህንን ዘመናዊ አውሮፕላን ማረፊያ በዛሬው ዕለት መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ባደረጉበት ወቅት ነው።   ጠቅላይ ሚኒስትሩ በንግግራቸው ላይ በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ በሁሉም አቅጣጫዎች ትላልቅ አውሮፕላኖችን ማስተናገድ የሚችሉ ወደ 30 የሚጠጉ የአየር ማረፊያዎች እንደሚገኙ ጠቁመዋል። የአየር ማረፊያዎቹ ስርጭት ሀገራዊ አንድነትን እና ልማትን እኩል ለማስፈን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ገልጸው፤በሰሜን 10፣ በምሥራቅ 5፣ በምዕራብ 7 እንዲሁም በደቡብ የሀገሪቱ ክፍል አዲሱን የነገሌ ገዳ አውሮፕላን ማረፊያን ጨምሮ 6 የአየር ማረፊያዎች መኖራቸውን በዝርዝር አብራርተዋል። የቦረና ሕዝብ የኦሮሞን ማንነት፣ባህልና እሴት ጠብቆ ያቆየ እንዲሁም ከጉጂና ባሌ ማኅበረሰቦች ጋር በትብብር የኖረ ታላቅ ሕዝብ መሆኑን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለሰላም ወዳዱ የቦረና እና ጉጂ ሕዝብ ልማት ብንዘገይም ደርሰንለታል ብለዋል።   አዲሱ የመሠረተ ልማት አውታር አካባቢው ከአዲስ አበባ ካለው የርቀት ስፋት አንጻር የሚፈጥረውን ተግዳሮት በመቅረፍ፤ ለአካባቢው ማኅበረሰብ ዘርፈ-ብዙ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የገነባው ይህ አዲስ አውሮፕላን ማረፊያ እንደ ቦይንግ 737 ማክስ ያሉ ዘመናዊና ግዙፍ አውሮፕላኖችን የማስተናገድ ሙሉ አቅም እንዳለውም ተናግረዋል። በሳምንት ሦስት የበረራ ቀናትን የሚያስተናግደው ይህ አየር ማረፊያ፤ የክልሎችን ኢኮኖሚያዊ አቅም ከማነቃቃት ባለፈ የድንበር ተሻጋሪ የንግድ ልውውጥንና የቱሪዝም ዘርፍን ለማሳደግ ታላቅ ራዕይ የሰነቀ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል። የአየር ማረፊያውን ለገነባው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። በቀጣይም ፍትሐዊ ተጠቃሚነትንና የገበያ ትስስርን መሠረት ያደረጉ አዳዲስ የአየር ማረፊያዎች ግንባታ በተለይም በደቡብና ምሥራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች ተጠንተው እንደሚቀጥሉም ጠቁመዋል። ለዚህም ስኬት ሰላም ወዳዱ የጉጂና የቦረና ሕዝብ የጀመረውን የልማት ትብብር አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
የቦረና ሕዝብ ከተረጅነት ነፃ መውጣቱ በተግባር የታየ ትልቅ ለውጥ ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 200
አዲስ አበባ፤ግንቦት 19 /2018 (ኢዜአ)፦የቦረና ሕዝብ ያሳየው የታታሪነትና የሥራ ወዳድነት መንፈስ የተፈጥሮ ጸጋን ተጠቅሞ ከረሃብ መውጣት እንደሚቻል ትልቅ ማረጋገጫ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ያመለከቱት በምስራቅ ቦረና ዞን ሊበን ወረዳ በሜካናይዜሽን የታገዘውንና በክላስተር እየለማ የሚገኘውን ሰፊ የስንዴ ማሳ በጎበኙበት ወቅት ነው።   የአካባቢው ማህበረሰብ ከጥቂት ዓመታት በፊት ይደርስበት ከነበረው ተደጋጋሚ የድርቅ አደጋና የውኃ እጥረት ፈተና ተላቆ፣ በአሁኑ ወቅት በአረንጓዴ ልማት አዲስ ምዕራፍ እየጻፈ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል። ቀደም ሲል እስከ 90 በመቶ የሚደርሰው የዞኑ ነዋሪ በሴፍቲኔት ድጋፍ ይተዳደር እንደነበርና ማህበራዊ ሁነቶች እንኳ ሳይቀሩ በእርዳታ እህል ይከናወኑ እንደነበር ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ዛሬ ላይ ግን ያ የድህነት ታሪክ ተቀይሮ የተረጅነት ምጣኔው ወደ ዜሮ መውረዱን ይፋ አድርገዋል። ይህ በአጭር ጊዜ ውስጥ የተመዘገበውና ማህበረሰቡን ከእርዳታ ጥገኝነት ሙሉ በሙሉ ያላቀቀው ስኬት በቃላት ሊገለጽ የማይችል ተዓምር መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮው አውድማ በሊበን ወረዳ ብቻ 250 ሺህ ሄክታር መሬት በስንዴ ሰብል መሸፈኑን ጠቁመው፤ የተሻሻሉ የውኃ አማራጮችን በመጠቀም ምርታማነቱን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚቻልና ይህም ከአገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ምርትን ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ዕድል እንደሚፈጥር አመላክተዋል። ቀደም ሲል የረድኤት እህል ይከፋፈልበት የነበረው ስፍራ ዛሬ ወደ ሰፊ የምርት ማዕከልነት ተለውጦ ማየት ታላቅ ደስታን የሚፈጥር መሆኑን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህ አይነቱ አመርቂ የልማት ተሞክሮ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎችም ሊሰፋ እንደሚገባ አሳስበዋል። በርትቶ በመስራት ከልመናና ከረሃብ መውጣት እንደሚቻል የቦረና ሕዝብ በተግባር ማሳየቱንም አክለዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማጠቃለያቸው፤ የቦረና ሕዝብ ያሳየው ታታሪነት እና የስራ ወዳድነት መንፈስ የተፈጥሮ ጸጋንና እውቀትን አቀናጅቶ በመጠቀም ረሃብንና ጥገኝነትን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስወገድ እንደሚቻል ትልቅ ማረጋገጫ የሰጠ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም