ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የመምህራንን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት የክልሉ መንግስት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ ያደርጋል
May 2, 2026 38
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ የመምህራንን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት የክልሉ መንግስት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ እንደሚያደርግ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለፁ፡፡ ‎አቶ ደስታ ሌዳሞ የክልሉ መምህራን ማህበር ለሚያስገነባቸው የመምህራን ሆስፒታል እና ሁለገብ ሕንጻዎች ግንባታ ሥራ የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል፡፡   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት መምህራን በክልሉ ሁለንተናዊ ዕድገት ላይ ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑንና በተለይ ከማህበሩ ጋር በመቀራረብ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የትምህርት ሥብራትን ለመጠገንና የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ እየተደረገ ባለው ጥረት ተጨባጭ ለውጥ እየታየ መምጣቱንም ተናግረዋል፡፡ የክልሉ መንግስት ለግንባታ ሥራው ማስጀመሪያ የሚሆን 50 ሚሊየን ብር ድጋፍ ማድረጉንና ሕንፃው ተጠናቆ ለአገልግሎት እስኪበቃ የክልሉ መንግስት ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡   የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንት ዮሐንስ በንቲ (ዶ/ር) በበኩላቸው መምህራን በትውልድ ግንባታ ውስጥ ተሳትፏቸው ከፍተኛ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ የመምህራን ኢኮኖሚያዊ አቅም እንዲሻሻል፣ ምቹ የሥራ አካባቢ እንዲኖራቸውና ጤናቸው በአግባቡ ተጠብቆ በበለጠ ትጋት እንዲሰሩ ለማስቻል ማህበሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ ፕሮጀክት ቀርጾ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   የሲዳማ ክልል መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንት ኢያሱ ፍቅሬ የክልሉ መምህራን ጠንካራ የትምህርት ሥርዓትን ለመገንባትና የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ከመንግስት ጋር በቅንጅት እየሰሩ ይገኛሉ ብለዋል። ማህበሩ ከ46 ሺህ በላይ አባላትን በሥሩ መያዙን ጠቁመው የመምህራን መታከሚያ ሆስፒታልና ሁለገብ ሕንጻዎቹ የረጅም ጊዜ ጥያቄ ሆነው መቆየታቸውን አስታውሰዋል፡፡ በክልሉ በየደረጃው በመንግስት እየተደረገላቸው ላለው ያልተቋረጠ ድጋፍ አመስግነው የማህበሩ አባላት ትውልድ የመቅረጽ ሀላፊነታቸውን በበለጠ ተናሳሽነትና ትጋት አጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። ለመምህራን ሆስፒታል የሚገነባው ሕንጻ ባለ 6 ወለል መሆኑን ገልጸው፣ ሁለገብ ሕንጻው ባለ 12 ፎቅ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሕንጻዎቹ በ1ሺህ 200 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ እንደሚያርፉ ገልጸው ለግንባታቸውም በአጠቃላይ ከ900 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ እንደሚጠይቁ ገልጸዋል።
አርሶ አደሮች ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በወቅቱ መቅረቡ ለግብርና ሥራቸው ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን ተናገሩ
May 2, 2026 38
ወልቂጤ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ለበልግ ወቅት አዝመራ የአፈር ማዳበሪያ እና ምርጥ ዘር በወቅቱ ማግኘታቸው ለግብርና ሥራቸው ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን ኢዜአ ያነጋገራቸው የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ።   የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ወቅቱን ጠብቆ መቅረቡ ለግብርና ልማት ሥራቸው መሳካት ከፍተኛ ዐቅም መፍጠሩን የአበሽጌ ወረዳ አርሶ አደር ሰብስቤ ወልደሃዋርያት ተናግረዋል። ከአራት ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ማግኘታቸውን ገልጸው፤ እስካሁንም ሦስት ሄክታር መሬታቸውን በበቆሎ እና በማሽላ ምርጥ ዘር መሸፈናቸውን አስረድተዋል።   አርሶ አደር ፍቃደ ተበቃም የቀረበላቸውን የአፈር ማዳበሪያ ተጠቅመው ማሳቸውን በበቆሎ ዘር እንደሸፈኑ ገልጸዋል።   በዞኑ ከ82 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበልግ አዝመራ በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አበራ ወንድሙ ናቸው። በበልግ እርሻ በቆሎ፣ ማሽላ፣ ድንችና ሌሎች ሰብሎች እንደሚለሙ ጠቅሰው፤ እስካሁን 34 ሺህ ሄክታር ማሳ በድንች ዘር መሸፈኑን አረጋግጠዋል። በ46 ሺህ ሄክታር ላይ በቆሎ እንደሚለማ ጠቁመው፤ በግንባር ቀደም አርሶ አደሮችም በሄክታር ከ121 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ግብ ተጥሏል ብለዋል። የበልግ አዝመራ ልማቱን ለማሳካት 8 ሺህ 200 ኩንታል የበቆሎ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ ቀመቅረቡን ጠቁመዋል። ከሰው ሠራሽ ማዳበሪያ በተጨማሪ የተፈጥሮ ማዳበሪያ (ኮምፖስት) ተዘጋጅቶ ለግብርና ሥራው ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
መንግሥት ሀገራዊ ብልፅግናን የሚያፋጥኑ መዋቅራዊ ለውጦችን በስኬት እያከናወነ ይገኛል -የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
May 2, 2026 39
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 24/2018 (ኢዜአ)፦ መንግሥት ዘላቂ አጀንዳዎች ላይ በማተኮር ሀገራዊ ብልፅግናን የሚያፋጥኑ መዋቅራዊ ለውጦችን በስኬት እያከናወነ እንደሚገኝ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለጸ። አገልግሎቱ ባወጣው መግለጫ፤ መንግሥት የ'ዲጂታል ኢትዮጵያ'ን መነሻ ያደረገውና ግልጽነትን ያሰፈነው ዘመናዊ የመንግሥት አገልግሎት ሥርዓት በተግባር ፍሬ እያፈራ ያለ ታላቅ ሀገራዊ ሽግግር ነው ብሏል። በተለይም የቴሌኮም ዘርፍ ሊበራላይዜሽን ርምጃዎች የውድድር መንፈስን በመፍጠር የኢንተርኔትና የዲጂታል ትስስር ተደራሽነትን በከፍተኛ ፍጥነት ማሳደግ መቻሉን አመልክቷል። ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ፍትህን ለማስፈን ወሳኝ የሆነው የ"ፋይዳ" ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ ሥርዓትም በተሳካ ሁኔታ በመተግበር ላይ ይገኛልም ነው ያለው። ይህ ሥርዓት በአጭር ጊዜ ውስጥ በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ የፋይናንስ አካታችነትን ከማረጋገጡም በላይ የመንግሥትን ሀብት ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ለማከፋፈል እና ድጋፍ ለሚሹ የሕብረተሰብ ክፍሎች በቀጥታ እንዲደርስ በማድረግ ረገድ የላቀ አስተዋፅዖ የሚያበረክት ዳግማዊ ሕዳሴያችን ነው ሲልም አብራርቷል። የዜጎችን እንግልት ለማስቀረት እና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን የመንግሥት አገልግሎቶችን ወደ ዲጂታል አማራጭ የማሸጋገሩ ጥረት ሌላው ተጨባጭ ስኬት የተመዘገበበት መስክ ነው ያለው መግለጫው፤ የተለያዩ የሚኒስቴሮች የፌዴራል ተቋማት አገልግሎቶቻቸውን በኤሌክትሮኒክስ መንገዶች መስጠት በመጀመራቸው የቢሮክራሲ ውጣ ውረዶች በከፍተኛ ደረጃ እንዲቀንሱ ተደርጓል ብሏል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ የመንግሥት ክፍያዎችን በዲጂታል የክፍያ ሥርዓቶች እንዲፈጸሙ መደረጉ የምዝበራና የሙስና ቀዳዳዎችን በመዝጋት፣ የመንግሥትን ገቢ በከፍተኛ መጠን ለማሳደግ እና ሀብትን ለልማት ስራዎች ለማዋል አስቻይ ዐውድ መፍጠር አስችሏል። ለዚህ የዲጂታል ሽግግር የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ዋነኛ ምሰሶ ሲሆን፤ ዘርፉ በተለይም ለወጣቱ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ አስረድቷል። በቴክኖሎጂ ፈጠራ ላይ ለተሰማሩ ወጣቶች (ስታርትአፖች) ምቹ ምህዳር ከመፍጠር አኳያ የሕግ ማዕቀፎች መሻሻላቸው እና የፋይናንስ አቅርቦት አማራጮች መስፋፋታቸው ኢትዮጵያ በቀጣይ ዓመታት የአፍሪካ የቴክኖሎጂ ማዕከል እንድትሆን ጠንካራ መሰረት ጥሏልም ነው ያለው አገልግሎቱ በመግለጫው። መንግሥት ለዘርፉ የሰጠው ልዩ ትኩረት ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎችን ትኩረት ስቦ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ረገድ አበረታች ውጤቶች እያስመዘገበ መቀጠሉንም አመልክቷል።
ኢንተርፕራይዞቹ በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው
May 2, 2026 50
ሆሳዕና፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- በመንግሥት የተደረገላቸው ድጋፍ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር እንዳስቻላቸው በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተለያየ የሥራ መስክ የተደራጁ ኢንተርፕራይዞች ገለፁ፡፡   በጉራጌ ዞን አረቅጥ ከተማ የወሄነት ዳቦ ማምረቻና መሸጫ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ወጣት መሰረት ወልዴ እንዳለችው፤ ኢንተርፕራይዛቸው ከአባላቱ አልፎ ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር ችሏል። ከሦስት ዓመት በፊት በመንግሥት በተመቻቸላችው የ50 ሺህ ብር ብድር የማምረቻና የመሸጫ ሼድን ጨምሮ በተሰጣቸው የሥልጠና ድጋፍ ወደ ሥራ መግባታቸውን አውስታለች። ማኅበሩ አሁን ላይ የአባላቱን ተጠቃሚነት ከማሳደግ አልፎ፤ ለ 25 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን እና ከ11 ሚሊየን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገቡን ለኢዜአ አረጋግጣለች።   በቡታጅራ ከተማ የሚገኘው የአድማሱ ቶርኖ ሥራዎች አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ሥራ አስኪያጅ ወጣት ዳዊት አድማሱ፤ ኢንተርፕራይዙ የአርሶ አደሩን ምርት አሰባሰብ ሂደት የሚያዘምኑ ማሽኖችን መሥራቱን ገልጿል። ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ከመጠቀማቸው አልፎ፤ ለ13 ወጣቶችም የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ተናግሯል። ኢንተርፕራይዙ በ300 ሺህ ብር ሠራ መጀመሩን አውስቶ፤ አሁን ላይ ካፒታሉ 5 ሚሊየን ብር ደርሷል ብሏል።   የውኃ መሳቢያ ፓምፕ እና ሌሎች የፈጠራ ሥራዎችን ለገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን የገለጸው ደግሞ በሆሳዕና ከተማ የሚገኘው የአሚቼ ብረታ ብረትና እንጨት ሥራዎች ቴክኖሎጂ ሽግግር አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ተካልኝ ዓለሙ ነው። በተሰማሩበት ዘርፍ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ከመምጣቱ በተጨማሪ በቴክኖሎጂ ሽግግር ረገድ ሌሎች ወጣቶችን እያሰለጠኑ መሆኑንም አስታውቋል። በክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሙስጠፋ ኢሳ እንዳሉት፤ በአነስተኛ እና በመካከለኛ ደረጃ ለሚገኙ 3 ሺህ 620 አምራች ኢንተርፕራይዞች ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ነው። ኢንተርፕራይዞቹ ዘላቂና አስተማማኝ የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ለሀገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት የሚያበረክቱት አስተዋጽዖ ከፍተኛ መሆኑንም አመላክተዋል።
በከተማዋ ‎የተገነባው የመንግስት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር ሕንፃ ምቹ የሥራ ሁኔታ ለመፍጠርና ገቢን ለማጠናከር ያስችላል
May 2, 2026 55
ባህር ዳር፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ በባህር ዳር ከተማ ‎የተገነባው የመንግስት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር ሕንፃ ምቹ የሥራ ሁኔታን ለመፍጠርና ተጨማሪ ገቢን ለማጠናከር እንደሚያስችል የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ። በመንግስት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር በባህር ዳር ከተማ የተገነባው ባለ 9 ወለል ዘመናዊ መንትያ ሕንፃ ወደ ሥራ ገብቷል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በምረቃው እንደገለጹት ከጣና ሐይቅ በቅርብ ርቀት ላይ የተገነባው ሕንጻ በአካባቢው ከለማው የአረንጓዴ መዝናኛ ስፍራ ጋር ተዳምሮ የከተማዋን ገጽታ የቀየረ ነው። መንትያ ሕንፃው ከቢሮ አገልግሎት በተጨማሪ ለመዝናኛ፣ ለንግድ እንቅስቃሴ፣ ለስብሰባና ለቱሪዝም አገልግሎት የሚውል መሆኑን አመልክተዋል። ይህም ለተቋሙ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ በመሆን ኢኮኖሚያዊ አቅምን ከማጠናከር ባለፈ ምቹ የሥራ ሁኔታን እንደሚፈጥር ጠቁመዋል። በመንግስት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር የሰሜን ምዕራብ ሪጅን ጽህፈት ቤት ኃላፊ አስቻለው ሞላ በበኩላቸው መንትያ ሕንጻው ከ2 ቢሊየን ብር በላይ ወጭ የተገነባ መሆኑን ገልጸዋል። በጠቅላላ 2ሺህ 640 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያረፈው ሕንጻ ከቤዝመንት በተጨማሪ ዘጠኝ ወለል እንዳለውና ግንባታውም በተያዘለት ጊዜ እንደተጠናቀቀ ተናግረዋል። ሕንጻው ለተለያዩ አግልግሎቶች የሚውል በርካታ ክፍሎች ያሉትና ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች የተሟሉለት መሆኑንም አመልክተዋል። የሕንጻው ግንባታ ተቋሙ ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት እንዲሰጥ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑንም አክለዋል።
ሚኒስቴሩ የንግድ ስርዓቱን ከማዘመን ባለፈ በማህበራዊ ኃላፊነት ዘርፍ በርካታ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ ነው
May 2, 2026 61
ሮቤ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ የንግድ ስርዓቱን ከማዘመን ባለፈ ማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት በርካታ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ገለጸ። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከተጠሪ ተቋማቱ ጋር በመቀናጀት በባሌ ሮቤ ከ37 ሚሊዮን ብር በላይ ያስገነባቸው መኖሪያ ቤቶችን ለአቅመ ደካሞች አስረክቧል። የተገነቡት 20 መኖሪያ ቤቶች እያንዳንዳቸው የራሳቸው መሰረተ ልማትና የመኖሪያ ቁሶቁሶችን የተሟላላቸው መሆኑም ነው የተገለፀው። በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ የተገኙት የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ተቋሙ የንግድ ስርዓቱን ከማዘመን ባለፈ የማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። ከዚህ ውስጥም በሀገሪቱ የተለያዩ ክልሎች ተመሳሳይ ዜጋ ተኮር ልማቶችና አገልግሎቶችን በማካሔድ ማሕበረሰቡን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ነው የገለጹት። ዛሬ በባሌ ሮቤ ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁት እነዚሁ ፕሮጀክቶች የዚሁ ጥረት ማሳያ መሆናቸውን አመልክተዋል። ፕሮጀክቶቹ በተለይ የአቅመ ደካማ ወገኖች የመኖሪያ ቤት ችግርን የሚቀርፉ ከመሆናቸው ባሻገር ፤ በዘርፉ የተያዙ ሀገራዊ ግቦችን ከማሳካት መንፃር ጉልህ ድርሻ ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የሚያካሒደውን የበጎ አድራጎት እንቅስቃሴ ይበልጥ የሚያጠናክሩና ቀጣይነት ያላቸው መሆናቸውንም አንስተዋል። ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት በራሳቸውና ሌሎች አካላትን በማስተባበር የገነቡትን ዲጂታል መፀሐፍት ቤት ለቀድሞ ትምህርት ቤታቸው የሮቤ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አስረክበዋል። የመጽሃፍት ቤት ግንባታው የከተማዋን ወጣቶችና ተማሪዎች የንባብ ባህል ይበልጥ የሚያሳድግ ሲሆን የልጅነት ሕልማቸውንም ለማሳካት ያስቻላቸው መሆኑንም ገልፀዋል። የሮቤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዲኖ አሚን በበኩላቸው ፤ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ለከተማዋ እድገትና ለአቅመ ደካማ ዜጎች ላደረገው ድጋፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። ከተማዋን ለነዋሪው ምቹና የንግድ ማእከል ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ውስጥ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እገዛ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ነው የገለጹት። ከልማቱ ተጠቃሚዎች መካከል ሼህ አልይ ከድርና ወይዘሮ ፋጡማ አብዳላ በበኩላቸው፣ የመኖሪያ ቤት ግንባታው ለዓመታት የነበረባቸውን የመጠለያ ችግር የሚቀርፍ መሆኑን ተናግረዋል።  
ሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትና ለኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ የሚያበረክት ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 2, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትና ለኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ የሚያበረክት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በርትተን ከሰራን፣ ጀምረን ከጨረስንና ክፍተቶችን እያየን መሙላት ከቻልን፣ ዘላቂና ተከታታይነት ያለው ዕድገት በማስመዝገብ የኢትዮጵያን ብልፅግና በአጭር ጊዜ ውስጥ እውን እናደርጋለን ብለዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ በሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ውስጥ የሚገኘውን "ጎበዝ ሶላር ሴል" ማምረቻንና ሌሎች ፋብሪካዎችን ጎብኝተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በግል ባለሀብት የተገነባው ሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ከጅማና ከኮምቦልቻ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በሦስት እጥፍ የሚበልጥ ሲሆን፣ ከሀዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ጋር ደግሞ በመጠን የሚስተካከል ነው። የሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ሠላሳ ሼዶች ያሉት መሆኑን ጠቅሰው፤ ስፋት ያለው፣ በርካታ ሰዎችን የሚይዝና ለከተማ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ በመሆኑ፣ የግል ዘርፉ በኢንቨስትመንት መስክ ያለውን ሚና አጎልቶ የሚያሳይ ነው ብለዋል። በጨርቃጨርቅ ላይ ተመስርቶ የነበረው የኢንዱስትሪ ፓርኮች ምርት አሁን ላይ እንዲሰፋ በተከናወነው ተግባር፤ ሶላር፣ የኤሌክትሪክ ባጃጅ፣ ጫማና አልባሳትን የመሳሰሉ ምርቶች በኢኮኖሚ ዞኑ እንደሚመረቱ ተናግረዋል። በኢኮኖሚ ዞኑ ባሉ ሼዶች የተለያዩ ምርቶች መመረታቸው የገበያ ዕድልን የሚያሰፋ መሆኑንም አንስተዋል። በኢኮኖሚ ዞኑ ያለው "ጎበዝ ሶላር ሴል" ማምረቻ አሁን ላይ ሁለት ጊጋ ዋት እያመረተ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይ ዓመት ተጨማሪ ሁለት ጊጋ ዋት ማምረት ይጀምራል ብለዋል። የሶላር ሴል ምርት በአጭር ጊዜ ውስጥ መመረት የጀመረና አሁን ላይ እየሰፋ ያለ መሆኑንም ተናግረዋል። ሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን በአዲስ አበባ የሚገኝና በርካታ ሼዶች ያሉት በመሆኑ፣ በርካታ የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ዕድል ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ኢንዱስትሪ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለኢነርጂና ለአገልግሎት ዘርፍ ዕድገት የሚውል በመሆኑ፣ በበርካታ መንገዶች በኢኮኖሚው ላይ አስተዋፅኦ የሚያበረክት እንደሆነም ገልፀዋል። ለውጭ ምንዛሬ ግኝት፣ ለእውቀት ሽግግርና ለሌሎች ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች የሚውል በመሆኑ፣ ጥቅሙን አሟጦ ለመጠቀም የተሳካውንና የሚቀረውን በመለየት በትኩረት መሥራት እንደሚጠይቅ አንስተዋል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተግባራዊ ለውጥ እያስመዘገበና የኢንዱስትሪ ሽግሽግን እያመጣ ያለ መሆኑን ገልፀዋል። ይህን ማጠናከር ከተቻለ በቀጣዮቹ ዓመታት ኢትዮጵያ በብዙ መልኩ ራሷን የመቻል ዕድል እንዳላት የሚያመላክት መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የመጣውን ውጤት በማስፋትና በማሳደግ የኢትዮጵያን ብልፅግና ማረጋገጥ ከሁሉም የሚጠበቅ ዐቢይ ተግባር መሆኑን ገልፀዋል።
ለግብርና ኢንቨስትመንት በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ የዘርፉ ውጤታማነት እያደገ ነው
May 2, 2026 113
ቦንጋ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ ለግብርና ኢንቨስትመንት የተፈጠረ ምቹ ሁኔታ የዘርፉን ውጤታማነት እንዳሳደገው ግብርና ሚኒስቴር ገለፀ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በግብርና ኢንቨስትመንት ከተሰማሩ ባለሀብቶችና ባለድርሻ አካላት ጋር ዛሬ በቦንጋ ከተማ መክሯል። በግብርና ሚኒስቴር የግብርና ኢንቨስትመንትና ምርት ግብይት መሪ ሥራ አስፈፃሚ ደረጀ አበበ እንደገለጹት መንግስት የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና የግል ባለሀብቱን ለማበረታታት የግብርናና ገጠር ልማት ፖሊሲ ቀርፆ ተግባራዊ አድርጓል።   ለዚህም ከግብዓት አቅርቦት ጀምሮ የተለያዩ የህግ ማዕቀፎችን በማሻሻል ለግል ባለሀብቱ በርካታ ማበረታቻዎችን በማድረግ ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል። የግብርና ኢንቨስትመንት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለውጭ ምንዛሬ ግኝትና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ የተለያዩ ምርቶችን ለማምረት አስተዋጽኦው የጎላ መሆኑንም አንስተዋል። ባለሀብቶች በገቡት ውልና በፖሊሲው በተቀመጠው መሰረት የወሰዱትን መሬት በአግባቡ ማልማት፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ በሰፊው መስራት እና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በትኩረት እንዲሰሩም አሳስበዋል። የመድረኩ ዓላማም በዘርፉ የተሰማሩ ባለሀብቶችን ችግር ለይቶ መፍትሄ ማበጀት፣ ትልልቅ የምግብ ዘይት አምራቾች በእርሻ ዘርፍ እንዲሳተፉ ማድረግና በሌሎች ጉዳዮች ላይ በመምከር ዘርፉን ይበልጥ ማጠናከር መሆኑንም ገልጸዋል።   ግብርና ለሀገር ኢኮኖሚ ያለዉ ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ሀላፊ አስራት አስፋ ናቸው። ባለፉት ጊዜያት በዘርፉ በተሰሩ ስራዎች የተመዘገቡ ውጤቶችን ለማጠናከር ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡ በተለይም ባለሀብቶች በግብርና ኢንቨስትመንት ላይ እንዲሰማሩ ከፋይናንስ አቅርቦት ጀምሮ በርካታ ድጋፎች በተሻለ መልኩ እየተደረጉ ነው ብለዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ በተሰጠ ትኩረት 544 ባለሀብቶች በግብርናው ዘርፍ መሰማራታቸውንና የዘርፉ ፍሰት በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መሆኑን ገልጸዋል። በዘርፉ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች 177ሺህ ሄክታር መሬት መመቻቸቱንና የህግና የአሰራር ማእቀፎች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።   በክልሉ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ በተሰራው ስራ የተሻለ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትልና የኢንቨስትመንት ዘርፍ ሀላፊ ከበደ ተስፋዬ ናቸው። ባለሀብቶቹ በቡና፣ በሰብል፣ በሻይ ልማት እንዲሁም በቅባት እህሎችና በሌሎች የግብርና ልማት ስራዎች መሰማራታቸውን አንስተው፣ ከእነዚህም ውስጥ 93ቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ወደ ስራ የገቡ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች ናቸው ብለዋል።
ኢትዮጵያ የአፍሪካ የታዳሽ ኃይል ማዕከል የመሆን ጉዞዋን አጠናክራ ቀጥላለች
May 2, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአህጉሪቱ የታዳሽ ኃይል ልማት ማዕከልነቷን ለማረጋገጥ በጀመረችው ጉዞ ያስመዘገበቻቸውን ተጨባጭ ውጤቶች አጠናክራ መቀጠሏን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ገለጸ።   ኢትዮጵያ በታዳሽ የኃይል ምንጮች ላይ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም፣ የአፍሪካ ህብረትን የ2063 አጀንዳ ለማሳካትና አህጉሪቱን በኤሌክትሪክ ኃይል ለማስተሳሰር ቁልፍ ሚና እየተጫወተች ትገኛለች። አሁን ላይ ተግባራዊ እየሆኑ ያሉት የቀጣናው የኃይል ሽያጭ ስምምነቶችም፣ ሀገሪቱ የጀመረችው የብልፅግና ጉዞ በተጨባጭ ውጤት የታጀበ መሆኑን የሚያረጋግጡ ናቸው። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ የአይሻ 2 እና የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫዎች በስኬት ተጠናቅቀው ወደ ሥራ በመግባታቸው የሀገሪቱ የኃይል ማምረት አቅም ከ9 ሺህ 752 ሜጋ ዋት በላይ ደርሷል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መረጃ እንደሚያሳየው በ2018 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት 24 ሺህ 970 ጊጋ ዋት ሰዓት ኃይል ለሀገር ውስጥና ለጎረቤት ሀገራት ለሽያጭ ቀርቧል። በበጀት ዓመቱ ለውጭ ሀገራት እና ለቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ከቀረበ የኃይል ሽያጭ 366 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ተገኝቷል። ይህም ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ138 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ብልጫ እንዳለው ነው የተመለከተው።   የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ሞገስ መኮንን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ አሁን ላይ የኤሌትሪክ ኃይል የምታመነጨው ከውኃ፣ ከንፋስ ኃይል፣ ከፀሐይ ሐይል እና ከጂኦተርማል ነው። የኃይል አማራጭን ይበልጥ በማስፋት በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኃይል አቅርቦት ለመገንባት እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ የታዳሽ ኃይል ማዕከል ለመሆን የያዘችው ርዕይ በተጨባጭ ከጎረቤት ሀገራት ጋር በተፈጠረው የኢነርጂ መሠረተ ልማት ትስስር እየታየ መሆኑን ገልጸዋል። ከሱዳን፣ ከጅቡቲ፣ ከኬንያና ከታንዛኒያ ጋር የኃይል ሽያጭ ግንኙነት መጀመሩን ጠቅሰው፤ ይህም የሀገሪቱን በጋራ መልማት የሚለውን የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ እውን ከማድረግ ባለፈ በመተማመን ላይ የተመሰረተ ግንኙነት እንዲኖር ያደርጋል ብለዋል።   ይህ እንቅስቃሴ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት የአጀንዳ 2063 የመሰረተ ልማት ትስስር ግቦችን ለማሳካት ያላትን ግንባር ቀደም መሪነትና አስተዋጽኦ የሚያሳይ ነው ብለዋል። ከኃይል ሽያጭ የሚገኘው የውጭ ምንዛሬ ገቢ ለኃይል መሰረተ ልማቶች መስፋፋትና ጥገና ከፍተኛ እገዛ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። ለአብነትም የአይሻ ሁለት የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ግንባታ ወጪ በሀገር ውስጥ የፋይናንስ አቅም መሸፈኑን ጠቅሰው፤ ይህም የኃይል ተደራሽነትን ለማሳደግና ከብክለት ነጻ የሆነ ኢኮኖሚ ለመገንባት ለሚደረገው ጥረት ትልቅ አቅም ሆኗል ብለዋል።   ኢትዮጵያ የኃይል ሽያጭ ግቧን ከጎረቤት ሀገራት ባለፈ እስከ ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራት ድረስ የማድረስ ሰፊ ዕቅድ ይዛ እየሰራች መሆኑንም ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅት ደቡብ ሱዳን የኃይል ፍላጎት በማሳየቷ የመግባቢያ ስምምነት ተፈርሞ በባለሙያዎች ደረጃ ዝርዝር ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። በተመሳሳይ ሶማሊያ የኃይል ፍላጎት እንዳላት የገለጹት ዳይሬክተሩ፤ የሌሎች ሀገራትን የኃይል መስመር በመጠቀም ድንበር ለማይጋሩ ሀገራት ጭምር ኃይል ለማቅረብ ዕቅድ መኖሩን አረጋግጠዋል።
የሌማት ትሩፋት ንቅናቄ ምርታማነትን በእጥፍ ማሳደግ አስችሏል
May 2, 2026 122
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ በመላው ሀገሪቱ በስፋት እየተከናወነ የሚገኘው የሌማት ትሩፋት ንቅናቄ ምርታማነትን በእጥፍ ማሳደግ ማስቻሉን ግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር በኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የተመጣጠነ ምግብ እጥረትን ለመቅረፍ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት ይፋ የተደረገ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው። ይህ የልማት ዕቅድ በዋናነት የወተት፣ የዶሮ፣ የማር፣ የሥጋ እና የዓሣ ሀብት ልማትን በቤተሰብ ደረጃ በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ያለመ ነው። በገጠርና በከተሞች በስፋት እየተተገበረ የሚገኘው ንቅናቄው የዜጎችን የምግብ አጠቃቀም ባህል በመቀየርና ራስን በምግብ ለመቻል የሚደረገውን ጥረት በማፋጠን ረገድ እንደ ዋና የልማት ምሰሶ ተደርጎ ይወሰዳል። ኢትዮጵያ ያሏትን ጸጋዎች በአግባቡ መጠቀም ከቻለችና ካለማች፣ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች የቅንጦት ምግቦች ሳይሆኑ ከሌማት መጥፋት የሌለባቸው እንደሆነ ታምኖበት በስፋት እየተሰራ ነው።   በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳት እና ዓሳ ሀብት ዘርፍ መሪ ስራ አስፈፃሚ አዚዝ አያሌው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሌማት ትሩፋት እየተከናወኑ የሚገኙት ተግባራት በምግብ ራስን ለመቻል የሚያግዙ ናቸው። የሌማት ትሩፋት ተግባራቱ ውጤት እያስመዘገቡ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ይህም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ አስቻይ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ባለፉት አራት ዓመታት በወተት፣ በዶሮ፣ በማርና ዓሳ ሀብት ዘርፍ ምርቶችን በእጥፍ ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል። በዚህም ለዜጎች ሰፊ የስራ እድል መፈጠሩንና የህብረተሰቡ ገቢ እንዲጨምር ብሎም የሀገር ኢኮኖሚ እንዲያድግ ማስቻሉን ተናግረዋል። በእንቁላል፣ በወተትና በስጋ ምርት ኢትዮጵያ ቀድማ የጀመረችው እንቅስቃሴ አሁን ያለውን የዓለም የገበያ ቀውስ ለማረጋጋት ትልቅ አቅም መፍጠሩንም ጠቅሰዋል፡፡ የሌማት ትሩፋት ምርታማነት ቀጣይነት እንዲኖረው የባለሀብቱ ተሳትፎ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመው፤ ባለሀብቱ በዘርፉ እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል። በዘርፉ የተሰማሩ አምራቾች በበኩላቸው፤ በሌማት ትሩፋት በመሰማራት ቤተሰቦቻቸውን ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ የተሻለ ገቢ እንዲኖራቸው እንዳስቻላቸው ይናገራሉ። አስተያየታቸውን ከሰጡ መካከል የተካልኝ ከበደ እና ጓደኞቻቸው ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ ተካልኝ አየለ፤ በሌማት ትሩፋት ዘርፍ በመሰማራት ተጨባጭ ውጤት ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡ በሥራው በርካታ ዓመታትን ማስቆጠራቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም ከእንስሳቱ በሚያገኟቸው ምርቶች ከራሳቸው ባለፈ የአካባቢውን ነዋሪዎች ተጠቃሚ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። በመሆኑም ወጣቶች በዘርፉ በመሰማራት የተሻለ ገቢ እንዲኖራቸውና ተሳታፊ እንዲሆኑም ጥሪ አቅርበዋል። አቶ ዘመኑ ታረቀኝ እና ወይዘሮ ጸዳለ እሸቴ፤ በሌማት ትሩፋት የሚያገኙት ውጤት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመምጣቱ፣ ከራሳቸው የዕለት ገበታ ባለፈ ለሌሎች በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል።
የሌማት ትሩፋት ዘላቂ ተጠቃሚነታችን እንድናረጋግጥ አግዞናል - የመርሐ-ግብሩ ተሳታፊዎች
May 2, 2026 68
ገንዳውኃ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር መሳተፋቸው ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እንዳስቻላቸው በምዕራብ ጎንደር ዞን የሚገኙ ዜጎች ተናገሩ። የመተማ ዮሐንስ ከተማ ነዋሪ የሆነው ወጣት ሙሉ መርሻ ለኢዜአ እንደገለጸው፤ ከ2 ዓመት በፊት በ400 ሺህ ብር የጀመረውን የወተት ልማት ካፒታል አሁን ወደ 1 ነጥብ 6 ሚሊየን ብር አሳድጓል። ከ16 ላሞች የሚያገኘውን የወተት ምርትም ለገበያ በማቅረብ ዘላቂ ተጠቃሚነቱን እያረጋገጠ እንደሚገኝ ተናግሯል። በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር በመታቀፍ በአምስት በሬዎች የጀመረውን የማድለብ ሥራ ይህን አሃዝ ወደ 15 ማሳደጉን የገለጸው ደግሞ የገንዳ ውኃ ከተማ ነዋሪ ወጣት ቢትወደድ አዳነ ነው። በዚህም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ማረጋገጡን ጠቁሞ፤ ለውጤታማነቱም የባለሙያዎች ድጋፍና ክትትል ትልቅ ድርሻ እንዳለው አስታውቋል። በዶሮ ዕርባታ ሥራ በመሰማራት ከእንቁላል ሽያጭ ብቻ በወር እስከ 25 ሺህ ብር እንደሚያገኙ የገለጹት ደግሞ በከተማዋ በዘርፉ የተሰማሩት አስቴር ገበየሁ ናቸው። በወተት ልማት ዘርፍ ለመሰማርት ዝግጅት እያደረጉ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።   የምዕራብ ጎንደር ዞን እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ እያያው ታከለ እንዳሉት፤ ወጣቶችን በዘርፉ በማደራጀትና በግል ወደ ሥራ እንዲገቡ በስፋት እየተሠራ ነው። ባለፉት ዘጠኝ ወራትም ከ3 ሺህ 900 በላይ የኅብረተሰብ ክፍሎች 203 ሺህ የሚጠጉ በሬዎችን አድልበው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን የሚገኘውን የ“ጎበዝ ሶላር ሴል” ማምረቻን ጎበኙ
May 2, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፦‎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ በሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ውስጥ የሚገኘውን የ“ጎበዝ ሶላር ሴል” ማምረቻን ዛሬ ጎብኝተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ፋብሪካው በ2025 የኢንቨስትመንት ፎረም (Invest in Ethiopia Forum) አማካኝነት በተፈረመው ስምምነት መነሻ በ100 ሚሊየን ዶላር የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ የተቋቋመ መሆኑን አውስተዋል። በውጤታማ ድጋፍ እና ክትትል በስድስት ወራት ብቻ እውን የሆነው "ጎበዝ ሶላር ሴል" ማምረቻ ዘመናዊ ማሽኖች እና በቴክኖሎጂ የተዋቀረ ነው ብለዋል። ማምረቻው ለበርካታ ዜጎች የስራ እድልም መፍጠር መቻሉንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ አመልክተዋል።   በመጀመሪያ ምዕራፍ 2 ጌጋዋት ዓመታዊ የማምረት አቅም ያለው ፋብሪካው፣ የኢትዮጵያን የኃይል ፍላጎት ሙሉ በሙሉ ከታዳሽ ኃይል ለማድረግ የተጀመረውን ሀገራዊ ርዕይ እውን ለማድረግ ተደማሪ አቅም መፍጠሩን ነው ያብራሩት።   በዚሁ የኢንደስትሪ ፓርክ ውስጥ የሚገኘውን የጫማ ማምረቻ እና ንዑስ የኤሌክትሪክ ጣቢያን መመልከታቸውንም በመልዕክታቸው ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ENA
በመጋቢት እና ሚያዝያ 2018 ዓ.ም ወራት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ካከናወኗቸው ተግባራት መካከል…
May 2, 2026 124
በመጋቢት እና ሚያዝያ 2018 ዓ.ም ወራት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሳይንሳዊ የምርምር ልህቀት፣ በከተማ ልማት፣ በኢኮኖሚ ሪፎርም እና በቀጣናዊ ዲፕሎማሲ ዙሪያ ያተኮሩ የተለያዩ ከፍተኛ የሥራ ክንውኖችን አድርገዋል። ‎ ‎• የፕሮጀክቶች ምረቃ እና የሥራ ጅማሮ ‎የመጋቢት ወር በተለያዩ ዘርፎች በርካታ ግዙፍ ፕሮጀክቶች የተመረቁበት ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአርማወር ሀንሰን የምርምር ኢንስቲትዩት (AHRI) ውስጥ ዘመናዊ የምርምር ማዕከል መርቀዋል። ይህ ማዕከል 40 የላብራቶሪ ክፍሎችን እና በሀገር ውስጥ የሚመረቱ መድኃኒቶችን ጥራት የሚያረጋግጥ የባዮ-ኢኩቫለንስ (bioequivalence) ማዕከልን ያካተተ ነው። ‎ ‎በከተማ ልማት ዘርፍ፣ የሚያዝያ ወር በአገልግሎት እና በዲጂታል መሠረተ-ልማት ግንባታ ረገድ ጉልህ እመርታ የታየበት ወር ነበር። የአራዳ ፓርክ ፕሮጀክት ከፍተኛ የሆነ የከተማ ገጽታ ለውጥ የታየበት ሲሆን፤ ቀደም ሲል ችላ ተብለውና ለአደጋ ተጋልጠው የነበሩ ቤቶች የሚገኙበትን 40 ሄክታር መሬት ወደ ዘመናዊ ሁለገብ መዳረሻነት ቀይሮታል። ይህ የተቀናጀ የመሠረተ-ልማት እና የመሬት አጠቃቀም ውጤታማነት የታየበት ፕሮጀክት፣ የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ ከ700 በላይ ነባር ቤቶችን የማደስ ስራን አካቷል። ከዚህም በተጨማሪ በ5.7 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈውና የኦሊምፒክ ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት መሠረተ-ልማቶችን፣ የ15 የወርቅ ሜዳልያ አሸናፊዎችን ሃውልት እና ለተነሺ ነዋሪዎች ተብለው የተገነቡ 105 የንግድ ሱቆችን የያዘው የአዲስ ስፖርት ፓርክ በዚሁ ወር ተመርቋል። ‎ ‎የሀገሪቱን የኃይል አቅርቦት አቅም ለማሳደግ የ100 ሜጋ ዋት የአሰላ የነፋስ ኃይል ማመንጫ ተመርቋል። በተጨማሪም በሀዋሳ የቶዮ ምዕራፍ 2፣ የኦሪጂን እና የሉሚንቴክ የሶላር ፋብሪካዎች ሥራ ጀምረዋል። እነዚህ ፋብሪካዎች ከአዲሱ የኤች.ዜድ (HZ) ጋዝ ፋብሪካ ጋር በመሆን በዓመት 11.3 ጊጋ ዋት ንጹህ ኃይል ያመነጫሉ ተብሎ ይጠበቃል። ‎ ‎በቱሪዝም ዘርፍ፦ በገበታ ለትውልድ መርሃ-ግብር የተገነባው የሀሮ ደንዲ ሎጅ በይፋ ተመርቋል። በመጨረሻም፣ እንደ መታወቂያ ምዝገባ እና የሥራ ፈቃድ ያሉ መሠረታዊ የመንግሥት አገልግሎቶችን በቀጥታ ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ የታለመው የመሶብ ተንቀሳቃሽ የአውቶቡስ አገልግሎት ስራ ጀምሯል። ‎ ‎• ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአፍሪካ ኅብረት የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እና የዲጂታል ጤና መሪ ሆነው የተሾሙት በያዝነው የሚያዝያ ነው። ይህ ኃላፊነት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሉዓላዊነት፣ ለውጤታማነት እና ለአካታች ዕድገት ቁልፍ መሣሪያ የሆኑትን የፈጠራ ሥራዎችን እና የዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን በማሳደግ ረገድ እያሳዩት ያለውን የአመራር ጥበብ እውቅና የሰጠ ሲሆን ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ንቁ አመራር ሰጪነት በዲጂታላይዜሽን ዘርፍ ያስመዘገበችውን ጉልህ ስራ የሚያሳይ ነው። ‎• የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የአፈጻጸም ግምገማ፦ ‎ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሦስተኛውን የ100 ቀናት የሥራ አፈጻጸም እና የዘጠኝ ወራት ሪፖርት ግምገማ መርተዋል። በዚህም የሀገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት 9.2 በመቶ መድረሱ የተገለጸ ሲሆን፣ በቀጣዩ ዓመት ደግሞ ወደ 10.2 በመቶ እንደሚያድግ ይጠበቃል። ሪፖርቱ በመንግሥት የልማት ድርጅቶች ላይ የተመዘገበውን ስኬታማ ሽግግር በዝርዝር ያሳየ ሲሆን፣ ቀደም ሲል በቢሊዮን የሚቆጠር ብር ኪሳራ ያስመዘግቡ የነበሩ ተቋማት በአሁኑ ወቅት 2.1 ትሪሊዮን ብር ገቢ ወደ ማስገባት ተሸጋግረዋል። ለዚህ ውጤት መገኘት ቁልፍ የሆነው የግሉ ዘርፍ የኢኮኖሚ እድገቱ ዋና መሪ እንዲሆን ቅድሚያ የሚሰጠው የሪፎርም አጀንዳ ነው። ይህም እንደ ካፒታል ገበያ ባሉ አዳዲስ የፋይናንስ ሥርዓቶች እና እያደገ በመጣው የመንግሥትና የግል ዘርፍ አጋርነት እየተደገፈ ይገኛል። ‎ ‎• የኢንዱስትሪ ስትራቴጂ ፦ ‎ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ በሰጡት ቃለ መጠይቅ፣ የሀገሪቱን ሉዓላዊነት ለማጠናከር አርቴፊሻል ኢንተለጀንስን (AI) እና ሮቦቲክስን በመጠቀም ወደ ቺፕስ እና ዳታ (ኢንዱስትሪ 4.0) መሸጋገር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። የሀገር ውስጥ ምርትን በማሳደግ የውጭ ምርቶችን መተካት የቻለው “ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ፣ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን የይዞታ መጠን ወደ 88 በመቶ ማድረሱን በስኬትነቱ ጠቅሰዋል። ከዚሁ ጋር በተያያዘ፣ ሰላማዊ የባሕር በር ማግኘት የሀገር የህልውና ጉዳይ መሆኑን አጽንኦት የሰጡ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ወደብ አልባ መሆኗ በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ እንዳትሆን ከፍተኛ የሎጂስቲክስ ወጪ እንደሚጨምርባት አስገንዝበዋል። ‎ ‎• ማህበራዊ ልማት እና የአካባቢ ጥበቃ አመራር፦ ‎“ማኅበራዊ ልማት እመርታ ለሀገር ግንባታ” በተሰኘው እና ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት የምክክር መድረክ ላይ፣ መንግሥት ባለፉት ስምንት ዓመታት ከ19.8 ሚሊዮን በላይ የሥራ ዕድሎች መፈጠራቸውን እና ይበልጥ ተዓማኒነት ያለው ሥርዓተ-ትምህርት ተግባራዊ መደረጉ ተገልጿል። በጤናው ዘርፍም በቅደመ መከላከል እና አክሞ ማዳን፤ መካከል የተሻለ ሚዛን ለመፍጠር ለ30 ዓመታት ያገለገለው ፖሊሲ እንዲሻሻል ተደርጓል። በአካባቢ ጥበቃ ረገድም ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ በ2027 የሚካሄደውን የኮፕ32 (COP32) ጉባኤን ለማስተናገድ ቅድመ ዝግጅት የጀመረች ሲሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩም ዝግጅቱ ከሀገራዊው የአረንጓዴ ልማት ግቦች ጋር የተጣጣመ መሆኑን እንዲያረጋግጥ ብሔራዊ አስተባባሪ ኮሚቴውን ሰብስበው አቅጣጫ ተሰጥተዋል። ‎ ‎• ዲፕሎማሲ እና ቀጣናዊ ትስስር፦ ‎ኢትዮጵያ የብሩንዲ፣ የላይቤሪያ፣ የደቡብ ሱዳን እና የሞዛምቢክ ፕሬዝዳንቶችን ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ያስተናገደች ሲሆን፤ ይህም በመከላከያ፣ በጤና፣ በትምህርት እና በዲጂታል መሠረተ-ልማት ዘርፎች ላይ ያተኮሩ በርካታ የመግባቢያ ስምምነቶች እንዲፈረሙ አስችሏል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከአውሮፓ ህብረት ዓለም አቀፍ አጋርነት ኮሚሽነር፣ ከአፍሪካ ኤክስፖርትና ኢምፖርት (Afrexim) ባንክ ፕሬዝዳንት፣ እንዲሁም ከፖርቹጋል የውጭ ጉዳይ እና የሀገር ውስጥ ሚኒስትር ጋር ተወያይተዋል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትሩ የጅቡቲ ሪፐብሊክ የውጭ ጉዳይ እና ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስትርን በመቀበል በሁለትዮሽ ትብብሮች ዙሪያ የመከሩ ሲሆን፤ ከአፍሪካ የበሽታ መቆጣጠሪያና መከላከያ ማዕከል (Africa CDC) ዋና ዳይሬክተር ጋር ደግሞ በአፍሪካ ህብረት ሰው ሰራሽ አስተውሎት እና ዲጂታል ጤና ረገድ የተሰጣቸውን ሚና ጨምሮ ሰፋ ባሉ ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተዋል። ‎ ‎በሀገር ውስጥ ጉዳይ፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት ከሆኑት ሌተናል ጄነራል ታደሰ ወረደ ጋር በመገናኘት ዓመታዊ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን የገመገሙ ሲሆን፣ የፕሬዝዳንቱን የሥራ ዘመን ለተጨማሪ አንድ ዓመት በይፋ አራዝመዋል። ‎ ‎የሚያዝ ወር የትንሳኤ በዓል የተከበረበት በመሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የማዕድ ማጋራት ፕሮግራም በማዘጋጀትና አነስተኛ ገቢ ላላቸው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት ሠራተኞች የቁሳቁስ ድጋፍ በማጋራት ተጠናቋል። #EthiopiaDelivers #PMOEthiopia
የክልሉን ከተሞች ከተፈጥሮ ፀጋዎቻቸው የሚያሰናስል የኮሪደር ልማት እየተከናወነ ነው
May 1, 2026 181
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከተሞችን ከተፈጥሮ ፀጋዎቻቸው የሚያሰናስል አስደናቂ የኮሪደር ልማት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኮሪደር ልማት የኢትዮጵያ ከተሞችን ለነዋሪዎችና ኢንቨስትመንት ምቹ ምኅዳር በመፍጠረ ከፍተኛ ጠቀሜታ እያበረከተ ነው። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልም አሶሳ ከተማን ጨምሮ ሌሎች ከተሞችን በኮሪደር ልማት በማስዋብ ለነዋሪዎችና ኢንቨስትመንት ምቹ ምኅዳር የመፍጠር ሥራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት ስራ የከተማዋን የመሰረተ ልማት ፍላጎትን በማሟላት ውብ ገፅታ እያላበሳት መሆኑን ተናግረዋል። የኮሪደር ልማት የለውጡ መንግስት የከተሞችን ዳግም ውልደት ያበሰረበት ወሳኝ የልማት መርሃ ግብር መሆኑን አንስተዋል። ከ2017 ዓ.ም ጀምሮ የሚከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች የክልሉን ከተሞች መሰረተ ልማት በማሳለጥ ውብ ገፅታ እያላበሱ መሆኑን ጠቅሰዋል። በቀጣይም የኮሪደር ልማት ስኬቶችን የበለጠ በማስፋት ከተሞችን ለነዋሪዎችና ለኢንቨስትመንት ምቹ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በክልሉ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች የልማት ሥራዎችም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ከፍተኛ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ አልሚዎችም የክልሉን ከፍተኛ የኢንቨስትመንት ፀጋ በመጠቀም በተለያዩ መስኮች በስፋት እየተሰማሩ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይም በተለያዩ የኢንቨስትመንት አማራጮች መሰማራት ለሚሹ አልሚዎች ተገቢውን ድጋፍና ክትትል ለማድረግ በቁርጠኝነት እደሚሰራ አረጋግጠዋል።  
በክልሉ ለኩታ ገጠም እርሻ በተሰጠ ትኩረት በምርታማነት ላይ ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል
May 1, 2026 128
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዝያ 23/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የኩታ ገጠም እርሻ ምርታማነትን በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት ማምጣቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ(ዶ/ር) ተናገሩ። ክልላዊ የበልግ አዝመራ የመስክ ምልከታ መርሃ ግብር በወላይታ ዞን ዳሞት ፑላሳ ወረዳ ተካሂዷል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ሃላፊ መሪሁን ፍቅሩ(ዶ/ር) እንደገለጹት በክልሉ በበልግ አዝመራ 987 ሺህ ሄክታር ማሳ በዘር በመሸፈን ከ97 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ታቅዶ እየተሰራ ነው። በበልግ ወቅት እየለማ ካለው መሬት 354 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በኩታ ገጠም እርሻ እየለማ መሆኑንም ተናግረዋል።   በዞኑ አርሶ አደሩን በዘመናዊ እርሻ በማሳተፍ ወደ ሜካናይዜሽን እርሻ ለማሸጋገር እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ሳሙኤል ተሰማ ናቸው። በተለይ ወጣቶችን በማህበር በማደራጀት የኩታ ገጠም እርሻ ለማስፋፋት በተደረገው ጥረት በርካቶችን ውጤታማ ማድረግ መቻሉን አመልክተዋል። በበልግ አዝመራ በማህበር ተደራጅተው በኩታ ገጠም እርሻ ያለሙትን በቆሎ እየተንከባከቡ መሆናቸውን የገለጹት አርሶ አደር ኤርጋና ኤርሳዶ ናቸው። ወረዳው ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ እንዲሁም ሌሎች የግብርና ግብአቶችን ቀድሞ ማድረሱ ሥራቸውን ውጤታማ እንዳደረገው ተናግረዋል። ሌላኛው አርሶ አደር በዘነ ሀርኪሶ ምርጥ ዘር፣ ዩሪያ እንዲሁም ዳፕ ማደበሪያዎችን ቀድመው በማግኘታቸው የበልግ ወቅት የሰብል ልማት ሥራቸውን በአግባቡ እያከናወኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በዚህም ያለሙት በቆሎ ቡቃያ በጥሩ ቁመና ላይ መሆኑን ጠቅሰው የግብርና ባለሙያዎች እያደረጉት ያለው ድጋፍና ክትትል ለውጤታማነቱ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አንስተዋል።
በዞኑ የተከናወኑ የልማትና የህግ ማስከበር ስራዎች የህብረተሰቡን ዘላቂ ተጠቃሚነትን ያረጋገጡ ናቸው
May 1, 2026 127
ደብረብርሃን፤ ሚያዝያ 23/2018(ኢዜአ)፦ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተከናወኑ የልማትና የህገ ማስከበር ስራዎች የህብረተሰቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ያረጋገጡ መሆናቸውን የሰሜን ሸዋ ዞን እና የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ኃላፊዎች ገለጹ። የሰሜን ሸዋ ዞንና የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር የዘጠኝ ወር የልማትና የመልካም አስተዳደር እቅድ አፈጻፀማቸው ላይ ውይይት አካሂደዋል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ መካሻ ዓለማየሁ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የዞኑን ሰላም ከማስከበር ጎን ለጎን የተሳካ የኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ የልማት ስራዎችን ማከናወን ተችሏል።   በተለያዩ መድረኮች ማሕበረሰቡን በማወየየትም የመንግስትን የሰላምና የልማት ተግባራት እንዲገነዘብ በመደረጉ በከፍተኛ ሁኔታ ድጋፉን መስጠቱን ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥም በርካታ የታጠቁ ሀይሎች አመራሮችና አባላት የሰላም አማራጭን በመቀበል የተሃድሶ ስልጠና ወስደው ወደ ህብረተሰቡ እንዲቀላቀሉ ማድረግ ያስቻለ መሆኑን ለአብነት አንስተዋል። በአካባቢው የተገኘው ሰላም የግብርና፣ የትምህርት፣ የጤናና ሌሎች የልማት ስራዎችን በማከናወን የህብረተሰቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ማስቻሉን ተናግረዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ በድሉ ውብሸት በበኩላቸው፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ሰላምን ከማጽናት ጎን ለጎን 19 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ተደርጓል ነው ያሉት። በተጨማሪም ለ54 የኢንቨስትመንት ፕሮጀከቶች ለግንባታ የሚውል መሬት መስጠት መቻሉን ጠቁመው በዚህም ለ13 ሺህ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር ተችሏል ብለዋል። መሰብ የአንድ ማዕከል ህንጻ ግንባታን በማፋጠን የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል እየተሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በዚሁ ወቅት በማህበር ተደራጅተው የቆጠቡና ሌሎች የተቀመጡ መስፈርቶችን ላሟሉ ከአምስት ሺህ በላይ ነዋሪዎች የቤት መስሪያ ቦታ መሰጠቱን ነው የተናገሩት።
በአማራ ክልል የአምራች ኢንዱስትሪው ለዜጎች ተጠቃሚነትና ለምጣኔ ሃብት እድገት ጠንካራ መሰረት እያኖረ ነው
May 1, 2026 132
ደብረ ብርሃን፤ ሚያዝያ 23/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የአምራች ኢንዱስትሪው ለዜጎች ተጠቃሚነትና ለምጣኔ ሃብት እድገት ጠንካራ መሰረት እያኖረ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሐመድ(ዶ/ር) ገለጹ። "ኢትዮጵያ ታምርት፣ እኛም እንሸምት" በሚል መሪ ሃሳብ በደብረ ብርሃን ከተማ የባለድርሻ አካላት ምክክር መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ በተለይም አምራች ኢንዱስትሪዎች የምርት አቅማቸውን የማሳደግና በተለያዩ ምክንያቶች ምርት አቁመው የነበሩ ኢንዱስትሪዎች ወደ ምርት መግባት የቻሉበት መልካም አጋጣሚ መፈጠሩ ተነስቷል። ከዚሁ ጋር በተገናኘ የአማራ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሐመድ (ዶ/ር)፤ በክልሉ የአምራች ኢንዱስትሪው ለዜጎች ተጠቃሚነትና ለምጣኔ ሃብት እድገት ጠንካራ መሰረት እያኖረ መሆኑን ለኢዜአ ገልጸዋል። የኢንዱስትሪውን ምርታማነት ለማሳደግ ከአርሶ አደሮች ጋር የገበያ ትስስር እንዲፈጠር በማድረግ፣ የግብአት አቅርቦት ችግሮችን በመፍታትና ለኢንዱስትሪ ምርቶች ምቹ ሁኔታ በመፍጠር ለዘርፉ እድገትና ማንሰራራት በትጋት መሰራቱን አንስተዋል።   በተለይም ሰሊጥ፣ አኩሪ አተር፣ የቢራ ገብስ፣ ጥጥና ሌሎች ምርቶችን በጥራትና በብዛት በማምረት ለኢንዱስትሪዎች ግብአት እንዲሆኑ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም ዘርፉ ለዜጎች ተጠቃሚነትና ለምጣኔ ሃብት እድገት ጠንካራ መሰረት እያኖረ መሆኑን ጠቁመው በቀጣይም በተጠናከረ መልኩ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በዘርፉ የተሰማሩ ባለሃብቶችም ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ ለዜጎች የስራ እድል በመፍጠርና ማህበራዊ ኃላፊነታቸውን በመወጣት የላቀ ሚናቸውን እየተወጡ ይገኛሉ ብለዋል። መሰል መድረኮች የዘርፉን ልማት ለማሳለጥና የሚያጋጥሙ ማነቆዎችን ለመፍታት ወሳኝ መሆናቸውን የገለጹት በማምረት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ደሳለኝ አብርሃም እና ወይዘሮ ትንሳኤ ፍቃደ ናቸው። የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉን ለማነቃቃት የመንግስት ጥረት፣ ድጋፍና ክትትል የሚደነቅ መሆኑን አንስተው በዚህም ተጨባጭ ውጤት መምጣቱን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለአምራች ኢንዱስትሪው ማንሰራራት ሁነኛ መፍትሄ በመሆኑ በቀጣይም ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል።
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪ ተወዳዳሪነትን በማሳደግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ ነው
May 1, 2026 169
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪ ተወዳዳሪነትን በማሳደግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ለ4ኛ ጊዜ የሚካሄደው ኢትዮጵያ ታምርት ዓለምአቀፍ ኤክስፖን በማስመልከት ለመገናኛ ብዙኅን መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኢንዱስትሪ ዘርፍ ማነቆዎች መፍትሔ በመስጠት የምርታማነት አቅምን እያጎለበተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። 4ኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖም "ኢትዮጵያ ታምርት፤ ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሃሳብ ከሚያዝያ 25 እስከ 30/2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ አስታውቀዋል። የኤክስፖ ዋና ዓላማም የኢትዮጵያን ምርቶች በማስተዋወቅ፣ ፈጠራን ማበረታታት፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የልምድ ልውውጥን በመፍጠር ተጨማሪ የገበያ ዕድሎችን ማስፋት እንደሆነ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ምርታማነት አቅም ለዓለም በማስተዋወቅ የምርት ጥራትና ብዛትን የሚያሻሽል ልምድና ተሞክሮ የሚቀመርበት መሆኑንም አንስተዋል። በኤክስፖው 850 የንግድ ስምምነቶችን በማድረግ ከአምስት ቢሊየን ብር በላይ ግብይት ይፈፀማል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል። በአዲስ አበባ አዲስ ዓለምአቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ለአምስት ቀናት የሚቆየውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ከ150 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ዜጎች እንደሚጎበኙት አስታውቀዋል። ስታርታፖችም በኤክስፖው የሚሳተፉበትን ዕድል በማመቻቸት የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ከትልልቅ ኢንዱስትሪዎች ጋር እንዲያስተሳስሩ እንደሚደረግም ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት ኤክሰፖው ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ሚኒስትሩ ጠቁመዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖው የኢንዱስትሪ ምርቶችን ከማስተዋወቅ ባለፈ የፓናል ውይይቶች፣ የምርት ልማት ውድድሮች፣ የዕውቅና እና ሌሎች መርሃ-ግብሮች እንደሚከናወኑ በመግለጫው ተመላክቷል።
ለአርሶ አደሮች የገበያ ትስስር የመፍጠር ስራ ተጠናክሮ መቀጠል ይገባዋል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 1, 2026 80
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦ አርሶ አደሮች ያመረቱትን ምርት በጥራት ለገበያ ማቅረብ እንዲችሉ የተጀመረው የገበያ ትስስር ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ስር የሚተዳደረው የላሜ ዴይሪ ያስገነባውን የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ከንቲባዋ በመልዕክታቸው፤ ፋብሪካው የግሉ ዘርፍ በአግሮ-ኢንዱስትሪው ያለውን ተሳትፎ የሚያሳድግ መሆኑን ገልጸዋል። ጥራቱን የጠበቀ የወተት ምርትን በዓይነትና በብዛት ለከተማዋና ለሀገሪቱ ተጠቃሚዎች በስፋት በማቅረብ፣ የነባሩን የላሜ ዴይሪ ተደራሽነት እንደሚያሰፋም አመልክተዋል። በርካታ የቀንድ ከብት ቢኖርም በእሴት ሰንሰለት እና በምርታማነት ውስንነት ምክንያት የወተት አቅርቦቱ ላይ አሁንም እጥረት እንዳለ ተናግረዋል። ዛሬ በላሜ ዴይሪ የታየው ዘመናዊ በሆነ ሂደት የወተት ምርትን በብዛትና በጥራት እንዲሁም ጤናማና ያለ ማቀዝቀዣ ከ6 ወራት በላይ ሊቆይ በሚችል መልኩ ለገበያ የሚያቀርብ በመሆኑ በዘርፉ የሚታየውን የአቅርቦት ችግር በእጅጉ ያቃልላል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪም፤ አርሶ አደሮች ያመረቱትን ምርት በጥራት ለገበያ ማቅረብ እንዲችሉ የተጀመረው የገበያ ትስስር የመፍጠር ስራ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ከንቲባዋ አሳስበዋል።
የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 1, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018(ኢዜአ)፦ ሁሉን አቀፍ ብልፅግናን በማሳካት የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ስር የሚተዳደረው የላሜ ዴይሪ ያስገነባውን የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት፤ በሀገራችን ከፍተኛ የእንስሳት ሀብት ቢኖርም፥ በወተት ምርትና ምርታማነት እንዲሁም አቅርቦት ላይ ውስንነቶች መኖራቸውን ጠቅሰዋል። ይህ ደግሞ ዜጎች በቂ የወተት ምርት እንዳያገኙ በማድረግ በስርዓተ ምግብ ላይ የራሱ አሉታዊ ተጽዕኖ እንዳለው በመገንዘብ መንግሥት ለዘላቂ መፍትሔ ትኩረት መስጠቱን ገልጸዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት ትውልዱ የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝና ጤናማና አምራች እንዲሆን የወተት ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ተግባራትን ማከናወኑን ተናግረዋል። ላሜ ዴይሪ ባለፉት ጊዜያት በወተትና በወተት ተዋጽኦ አቅርቦት ላይ የራሱን አወንታዊ አስተዋጽኦ ሲያበረክት መቆየቱንም ጠቁመዋል። በዛሬው እለት የተመረቀው ፋብሪካ የድርጅቱን የወተት ማምረት አቅም በተደራሽነትና በጥራት እንደሚያሳድገው ተናግረዋል። ሁሉን አቀፍ ብልፅግናን በአጭር ጊዜ ውስጥ እውን በማድረግ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑንም ነው የገለጹት። በቀጣይም መሰል ስራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ጠቁመው፤ ከተማ አስተዳደሩ ዘርፉን ለመደገፍ ከመቼውም ጊዜ በላይ ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጠዋል። የሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፤ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተሟላለት ይህ ፋብሪካ የድርጅቱን የአገልግሎት ጥራት እንደሚያሳድግ ጠቅሰዋል። ፋብሪካው የወተት ተዋጽኦን ያለምንም ማቀዝቀዣ ለስድስት ወራት ማቆየት የሚያስችል መሆኑንም ገልጸዋል። በምረቃ መርኃ-ግብሩ ለወተት አምራቾች፣ አቅራቢዎችና ሌሎች በዘርፉ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት እውቅና ተበርክቷል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም