ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በልማት ስራዎች ላይ በንቃት ከተሳተፍን በራስ አቅም ሀገርን መገንባት እንደምንችል ተገንዝበናል - ወጣቶች 
Jan 23, 2026 47
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦በልማት ስራዎች ላይ በንቃት ከተሳተፍን በራስ አቅም ሀገርን መገንባት እንደምንችል ተገንዝበናል ሲሉ ወጣቶች ገለፁ። የፌዴራል ተቋማት ብልፅግና ፓርቲ የኢኮኖሚ ክላስተር ወጣቶች ክንፍ "የወጣቶች በጎ እይታ ለታላቋ ኢትዮጵያ " በሚል መሪ ሀሳብ የኤኤምጂ ኢዲአር የባቡር መስመር እና የእንዶዴን ደረቅ ወደብ የመሰረተ ልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል።   በጉብኝቱም ወቅት የኢትዮ ጅቡቲ ባቡር አክስዮን ማህበር የባቡር ትራንስፖርት እና ሎጅስቲክ ዘርፉን በማዘመን ለተጠቃሚዎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የሚከናውናቸውን ተግባራት የፕሮጀክቱ የስራ ሃላፊዎች ለጎብኚዎች ገለጻ አድርገውላቸዋል። የብልጽግና ፓርቲ የወጣቶች ክንፍ ዋና ጽህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ሃላፊ ገዛኸኝ አንዳርጌ በዚሁ ወቅት እንደገለጸው፤ በመንግስት ባለፉት የለውጥ ዓመታት ሀገርን ወደ እድገት የሚያሻግሩ የልማት ስራዎችን እየተከናወኑ ይገኛል። ወጣቶችም እነዚህን ተጨባጭ የልማት ስራዎች በማየት ነገ ለሀገራቸው የተሻለ ነገር ማበርከት እንዲችሉ ታስቦ የተዘጋጀ መርሀ ግብር መሆኑንም ተናግሯል።   በኢትዮጵያዊያንና በሀገር ሀብት እየተሰሩ ያሉት የልማት ፕሮጀክቶችን መመልከት በወጣቶች ዘንድ ትልቅ ተስፋ የሚያጭር መሆኑን ገልጿል። ይህም በቀጣይ ወጣቶች በሀገራቸው ልማት ላይ የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርጉ መነሳሳት የሚፈጥር ነው ብሏል። በፌዴራል ተቋማት አደረጃጀት የብልጽግና ወጣቶች ክንፍ የኢኮኖሚ ክላስተር ሰብሳቢ ወንድማገኝ ይርጋለም በበኩሉ፤ ሀገራችን በተለያዩ መስኮች የጀመረቻቸው የልማት ስራዎች ላይ የመጣውን ለውጥ ለማስቀጠል ወጣቱ ሀይል ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ በጉብኝታችን ተመልክተናል ብሏል።   በቀጣይም የሀገራችንን ብልፅግና በሚያረጋግጡ የልማት ስራዎች ላይ እንደ ወጣት የሚጠበቅብንን ማበርከት እንዳለብን የቤት ስራ ወስደናል ሲል ገልጿል። ኑሪያ ሁሴን እና ትዕግስት ሽፈራው በበኩላቸው፤ የኢትዮ ጅቡቲ ባቡር አክስዮን ማህበር ለዜጎች ፈጣን እና የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠት በሚያከናውናቸው የልማት ስራዎች ኩራት ተሰምቶናል ብለዋል።
የእንስሳት ግጦሽ መሬት ደኅንነትን በማስጠበቅ የአርብቶ አደሮችን ዘላቂ ተጠቃሚነት የበለጠ ማረጋገጥ ያስፈልጋል
Jan 23, 2026 68
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦የእንስሳት ሃብት የግጦሽ መሬት ደኅንነትን በማስጠበቅ የአርብቶ አደሮችን ዘላቂ ተጠቃሚነት የበለጠ ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና አካባቢ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል አጉ ደባን ገለጹ። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአውሮፓውያኑ 2026 የግጦሽ መሬትና አርብቶ አደርነት የማስተዋወቅ ዓመት እንዲሆን መወሰኑ ይታወሳል፡፡   የግብርና ሚኒስቴር፣ የመንግስታቱ ድርጅት፣ የዓለም አቀፍ የምግብና እርሻ ድርጅት እና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለሁለት ቀናት የሚቆይ "የግጦሽ መሬትና አርብቶ አደርነት ዓመት" ጉባኤ ማካሄድ ጀምረዋል። በጉባኤ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና አካባቢ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል አጉ ደባን እንደገለፁት፤ የግጦሽ መሬት ደኅንነትን በመጠበቅ የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት ማስቀጠል ያስፈልጋል።   አርብቶ አደሮች ከኋላቀር የእንስሳት ሃብት አስተዳደር በማላቀቅ አስተማማኝ የግጦሽ ምኅዳር ለመፍጠር ዘላቂ የተቋም አቅም መገንባት እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና ዓሳ ሃብት ሚኒስትር ዴዔታ ጽሕፈት ቤት ከፍተኛ አማካሪ አለማየሁ መኮንን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የግጦሽ መሬት እንክብካቤና ጥበቃ ለአርብቶ አደር ማህበረሰብ ወሳኝ ጉዳይ ነው ብለዋል።   ኢትዮጵያም ሀገር በቀል የዳበሩ ዕውቀትና ልምዶችን በመጠቀም የአርብቶ አደሮችን የእንስሳት የግጦሽ መሬት ለመጠበቅ አበረታች ውጤት እያስመዘገበች መሆኗን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የግጦሽ መሬት ሥነ-ምኅዳር ጥበቃም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋም የምግብ ዋስትናን በሚያረጋግጥ የአሰራር ሥርዓት የተደገፈ መሆኑን አስረድተዋል። የአርብቶ አደሮች ፎረም መስራችና የቦርድ ሰብሳቢ ሀጂ አብዲ አብዱላሂ ሀሰን፤ ጉባኤው የኢትዮጵያ የአርብቶ አደሮችን የእንስሳት ሃብት ተጠቃሚነት ለማሻሻል ጉልህ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል።   በተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት የኢትዮጵያ ምክትል ተወካይ ወርቂቾ ጃተኖ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ አርብቶ አደሮችን የግጦሽ መሬት ደኅንነት ለማረጋገጥ ድጋፍ እንደሚደረግ ገልጸዋል።   በኢትዮጵያ የአውሮፖ ሕብረት ፕሮጀክት ማናጀር ተሬሳ ጃለታ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ አርቦቶ አደሮችን ዘላቂ እንስሳት ግጦሽ መሬት አስተማማኝ ደኅንነት ለማስጠበቅ ይደግፋሉ።
የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶች ለትውልድ የሚተላለፉ ናቸው-የአፋሕድ አመራር አባላት
Jan 23, 2026 49
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶች ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ለትውልድ የሚተላለፉ መሆናቸውን የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) አመራር አባላት ገለጹ። የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) ከፍተኛ አመራር አባላት በአዲስ አበባ ከተማ የዓድዋ ድል መታሰቢያ፣ የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻና ሰው ተኮር የልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል።   የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) የውጭ ግንኙነት መምሪያ ኃላፊ ካፒቴን ማስረሻ ሰጤ ፤ አዲስ አበባን ለማስዋብ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ለትውልድ የሚተላለፉ ናቸው ብለዋል። በኮሪደርና መዝናኛ፣ በወንዝ ዳርቻና ቅርስ ጥበቃ ልማት የተመዘገቡ ስኬቶች መዲናዋን ዓለም አቀፍ ውብ ገፅታ በማጎናጸፍ ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ተጠቃሚነት ያረጋገጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በተለይም በቅርስና ታሪካዊ ሥፍራ ጥበቃ የልማት ሥራ ላይ የተመዘገቡ ስኬቶች ቀጣዩን ትውልድ በሚቀርጽ የአሰራር ሥርዓት ተውበው የተገነቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። መዲናዋን በማስዋብ ሂደት ድጋፍና አስተዋጽኦ ላበረከቱ የፌዴራል መንግስት፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና ባለድርሻ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል። የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) ኢትዮጵያ በታሪካዊ ጠላቶች ፊት አውራሪነት በግጭት እንድትቆይ የተሸረበውን ሴራ በማጤን የሰላም አማራጭ እንደተቀበለ ገልጸዋል።   በአማራ ክልል ላለፉት ዓመታት የተከሰተው ግጭትም ተማሪዎችን ከትምህርት ገበታቸው በማስተጓጎልና የመሠረተ ልማት ግንባታን በማቋረጥ እንቅፋት መፍጠሩን አስታውሰዋል። በስምምነቱ መሠረትም በጫካ የነበሩት ወደ ተዘጋጀላቸው ጊዜያዊ ማዕከል በማሰባሰብ የህዝብ ሰላምና የልማት አካል ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል። የመዲናዋ የልማት ስኬቶች ጉብኝት ኃላፊነት የወሰድንበት ነው ያሉት ካፒቴን ማስረሻ፤ በቀጣይም የአማራ ክልልን የመሰረተ ልማት ሥራ ለማስቀጠል እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል። የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) ወታደራዊ አስተዳደር ኃላፊ ረዳት ፕሮፌሰር እያሱ አባተ፤ በመዲናዋ በአጭር ጊዜ ውስጥ አስደናቂ የልማት ስኬት ተመዝግቧል ብለዋል።   የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶችም ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ተጠቃሚ ማድረጋቸውን በጉብኝታቸው እንዳረጋገጡ አስረድተዋል። የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) አመራርና አባላት የሰላም አማራጭን መቀበል ለቀጣይ ሀገራዊ ልማትና ለህዝብ ተጠቃሚነት አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው ገልጸዋል። የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) የስልጠና መምሪያ ኃላፊ መልካሙ ጣሴ፤ በአዲስ አበባ ከተማ የህዝብን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ ለውጦች ተመዝግበዋል ብለዋል።   በተለይም በሰው ተኮር ልማት የተገነቡ ፕሮጀክቶች ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን የማህበረሰብ ክፍሎች ተጠቃሚነት ያረጋገጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግሥት እና የአማራ ፋኖ ህዝባዊ ድርጅት (አፋህድ) መካከል የተደረገውን የዘላቂ ሰላም ስምምነት ማዕቀፍ ውጤታማ ለማድረግ የማስፈፀሚያ ስምምነት ትናንት ተፈርሟል።     በዚህም የአማራ ክልል የሰላምና ደህንነት ቢሮ ሃላፊ እሸቱ የሱፍ (ዶ/ር) እና የአማራ ፋኖ ህዝባዊ ድርጅት ወታደራዊ አስተዳደር መምሪያ ሃላፊ እያሱ አባተ (ረዳት ፕሮፌሰር) ስምምነቱን መፈረማቸው ይታወቃል።
የጉምሩክ አገልግሎት ምኅዳር የመድኃኒትና ሕክምና መሳሪያ አምራቾችን ምርታማነት እያጎለበተ ነው
Jan 23, 2026 56
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦የጉምሩክ አገልግሎት ምኅዳር የሀገር ውስጥ የመድኃኒትና ሕክምና መገልገያ መሳሪያ አምራቾችን ምርታማነት እያጎለበተ መሆኑን የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ገለጸ። የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን እና የመድኃኒትና የሕክምና መገልገያ መሳሪያ አምራች ኢንዱስትሪዎች ማኅበር በጉምሩክ አገልግሎቶች ዙሪያ በትብብር በሚሰሩባቸው የዕቅድ ሥራዎች ላይ ውይይት አካሂደዋል።   በዚሁ ወቅት የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አዝዘው ጫኔ፤ በሕግና የአሰራር ሥርዓት የተወሰዱ የማሻሻያ እርምጃዎች የጉምሩክ አገልግሎቱን እያሳለጡ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የሕግና የአሰራር ሥርዓት ማሻሻያውን ተከትሎም የመድኃኒት አምራችና የሕክምና መሳሪያ አምራቾችን የጉምሩክ አገልግሎት ስትራቴጂክ አጋርነት ማጠናከር እንዳስቻለ አንስተዋል። በዚህም ለሀገር ውስጥ የመድኃኒትና የሕክምና መሳሪያ አምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ምቹ የጉምሩክ አገልግሎት ምኅዳር በመፍጠር ምርታማነታቸውን እያሳደገ መሆኑን ተናግረዋል። በመድኃኒትና የሕክምና መሳሪያ አምራቾች፣ ላኪና አስመጪዎች የሚቀርቡ አገልግሎቶችን በማሳለጥ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያሳድግ ቀጣይነት ያለው ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግም አረጋግጠዋል። በቀጣይም በትብብር የሚሰራባቸውን የጋራ ዕቅዶችን በባለድርሻ አካላት በማዳበር ውጤት በሚያስገኝ አግባብ ተግባራዊ እንደሚሆኑ አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የመድኃኒትና የሕክምና መገልገያ መሳሪያዎች አምራች ኢንዱስትሪዎች ማኅበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ታደሰ ተፈሪ፤ የፋርማሲቲካል ዘርፍ የጉምሩክ አገልግሎቶች ማሻሻያ ለውጥ እያመጣ ነው ብለዋል።   የኮሚሽኑ የሕግና የአሰራር ማሻሻያም ለመድኃኒትና የሕክምና መገልገያ መሳሪያ አምራቾች የጉምሩክ አገልግሎት መሳለጥ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የዘርፉን ምርታማነት በማሳደግና አዳዲስ የኢንቨስትመንት ዕድሎችን በመፍጠር በዜጎች የጤና አገልግሎት ተጠቃሚነት ላይ ትልቅ አቅም እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። የሀገር ውስጥ የመድኃኒትና የሕክምና መገልገያ መሳሪያ አምራቾችም ከውጭ የሚያስገቧቸውን ጥሬ ዕቃዎች በፍጥነት የሚያስገቡበት ምቹ ምኅዳር መፍጠር እንዳስቻለም አንስተዋል።
የኮሪደር ልማት የከተማዋን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ አነቃቅቷል
Jan 23, 2026 63
ወልዲያ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በወልዲያ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት አማራጭ የመዝናኛ ቦታዎችን ከመፍጠር ባለፈ የከተማዋን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ያነቃቃ መሆኑን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። ዕድሜ ጠገቧ የወልዲያ ከተማ በኮሪደር ልማቱ ውብና አዲስ ገጽታን ተላብሳለች።   ከተማዋ ያላትን ጸጋ ወደ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ለመቀየርና የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል እያበረከተ ያለው ሚና የጎላ መሆኑን አንስተዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ነዋሪዎች መካከል አለበል እሸቱ፣ የኮሪደር ልማቱ በተጠናቀቀባቸው አካባቢዎች የተገነቡ የንግድ ሱቆች የከተማዋን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ አነቃቅተዋል ብለዋል።   የኮሪደር ልማቱ ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ታሳቢ ያደረገ አማራጭ የመዝናኛ ቦታዎችን መፍጠሩን የተናገሩት ደግሞ ያለው አሰፋ ናቸው። ልማቱ በጥራትና በፍጥነት መከናወኑንም አንስተዋል። የወልዲያ ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራሬ በበኩላቸው፣ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ በበጎ ከመቀየር ባለፈ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴው ላይ አዎንታዊ ሚና ማሳደሩን ተናግረዋል።   ከኮሪደር ልማቱ ፈጠራና ፍጥነትን ታሳቢ በማድረግ በህብረተሰብ ተሳትፎ እየተከናወነ መሆኑንም አንስተዋል። በከተማዋ ባለፈው አንድ ዓመት 2 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት መጠናቀቁን ጠቅሰው፣ ቀሪው የ2 ነጥብ 7 ኪሎ ሜትር ኮሪደር ልማት በቀጣዮቹ ሁለት ወራት ውስጥ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። በወልዲያ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ከ550 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ለዕውቀት ሽግግር ከፍተኛ ጠቀሜታ እያበረከተ ይገኛል።
በነቀምቴ ከተማ የህብረተሰቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ ነው
Jan 23, 2026 71
ነቀምቴ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በነቀምቴ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የህብረተሰቡን ኑሮ እያሻሻሉ መሆኑን መመልከታቸውን በከተማዋ ጉብኝት ያደረጉ የተለያዩ ክልሎች የውሃና ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊዎች ገለጹ። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት እቅድ አፈጻጸም በነቀምቴ ከተማ እያካሄደ ይገኛል። በግምገማ መድረኩ የተገኙ የተለያዩ ክልሎች የውሃ እና ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊዎች በነቀምቴ ከተማ እና አካባቢው እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል።   በጉብኝቱ ላይ የተሳተፉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የማዕድን እና ኢነርጂ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ መኮንን መኔዶ፣ የኮሪደር ልማት ስራ ከተሞችን እያነቃቃ መሆኑን ተናግረዋል። በነቀምቴ ከተማም ኮሪደርን ጨምሮ እየተከናወኑ ያሉ አጠቃላይ የልማት ስራዎች ከተማዋን ለነዋሪዎቿ ምቹ ማድረግ ማስቻሉን መመልከታቸውን ገልጸዋል።   ስራው ለከተማዋ ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር ያስቻለ መሆኑን ጠቅሰው ለሌሎች ከተሞችም ተሞክሮ የሚሆን መሆኑን አስረድተዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የውሃ፣ ኢነርጂ እና መስኖ ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ ዳዊት ሀይሉ፣ በአካባቢው የሰፈነው ሰላም የልማት እንቅስቃሴ እንዲፋጠን ማስቻሉን መገንዘባቸውን ጠቁመዋል።   በሌሎች ከተሞች የተጀመሩ የኮሪደር ስራዎች እና ከተማን የማዘመን ስራ በነቀምቴ ከተማም በጥሩ ሁኔታ እየተከናወነ መሆኑን ማየታቸውን አመልክተዋል። በነቀምቴ ከተማ የተመለከቱት የልማት እንቅስቃሴ ተስፋ የሚጣልበት መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የሀረሪ ክልል የውሃ እና ፍሳሽ ቢሮ ሀላፊ ተወካይ አቶ ኤርምያስ ተካልኝ ናቸው።   በተለይም የኮሪደር ልማት ስራ፣ የፍሳሽ ማስወገጃ እና ማጣሪያ ግንባታ እና የንፁህ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ለከተማዋ ትልቅ ጠቀሜታ የሚሰጡ መሆናቸውን አስረድተዋል። በተለይ የፍሳሽ ማስወገጃ እና ማጣሪያው በሀገሪቱ ጥቂት ከተሞች ብቻ የተጀመረ መሆኑን አንስተው ስራው ተሞክሮ የሚወሰድበት መሆኑን አመልክተዋል።   የጉብኝቱ ተሳታፊዎች መንግስት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን በሁሉም አካባቢዎች እየተገበረ መሆኑን መረዳታቸውን አንስተዋል።
በአስተዳደሩ በበጋ መስኖ ልማት 4 ሺህ ሄክታር መሬት በስንዴ ሰብል ተሸፍኗል
Jan 23, 2026 64
ደብረ ብርሃን፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር በበጋ መስኖ ከ4 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ ሰብል እየለማ መሆኑን የአስተዳደሩ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ መርሻ ዓይሳነው ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ተጨማሪ ምርት በማግኘት ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ ነው። በዚህም በተያዘው የበጋ ወራት በከተማ አስተዳደሩ 4 ሺህ 185 ሄክታር መሬት በስንዴ እየለማ መሆኑን ገልጸው፣ ከዚህም ከ64 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል ብለዋል። የበጋ መስኖ ስንዴ ልማቱን ምርታማነት ለማሳደግም የዘመናዊ ማዳበሪያ፣ የምርጥ ዘርና ሌሎች የምርት ማሳደጊያ ግብአቶች ጥቅም ላይ መዋላቸውን ተናግረዋል።   በተጨማሪም 101 የውሃ መሳቢያ ጀነሬተሮችን ለአርሶ አደሮች በማሰራጨትና በትራክተር ጭምር በመታገዝ ልማቱን ውጤታማ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ነው የገለጹት። በመስኖ ልማት ሥራው ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል ደምሴ አሰፋ እንዳሉት፤ባለፈው ዓመት በግማሽ ሄክታር መሬታቸው ላይ ስንዴ በመስኖ በማልማት ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ከ250ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ገልጸዋል።   ዘንድሮም ካለፈው ዓመት ተሞክሮ ወስደው ሥራቸውን በማስፋፋት በአራት ሄክታር መሬት ላይ በመስኖ ስንዴ እያለሙ መሆናቸውን ተናግረዋል። ሌላው የመስኖ ልማት ተሳታፊ ቄስ መንገሻ ተክለወልድ በበኩላቸው፤ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከመጣ ወዲህ የዝናብ ወቅትን ሳይጠብቁ በማምረት የምግብ ሉአላዊነታቸውን እያረጋገጡ መምጣታቸውን ተናግረዋል።   የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ከተጀመረ ወዲህ የስንዴ ምርታማነትን በማሳደግ የአገር ውስጥ ፍጆታን ከመሸፈን ባለፈ ለውጭ ገበያ መላክ መጀመሩ የሚታወስ ነው።
የአፍሪካ ህክምና ግብዓት አምራቾች አውደ ርዕይና ጉባኤ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን አቅም ለማስተዋወቅ የላቀ ሚና አለው
Jan 23, 2026 67
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህክምና ግብዓት አምራቾች አውደ ርዕይና ጉባኤ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን አቅም ለማስተዋወቅ የላቀ ሚና እንዳለው የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ፍሬህይወት አበበ ገለጹ። "ሶስተኛው የአፍሪካ ህክምና ግብዓቶች የንግድ፣ አውደ ርዕይና ጉባኤ 2026" ከመስከረም 25 እስከ 27 ቀን 2019 በአዲስ አበባ ይካሄዳል።   የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ፍሬህይወት አበበ አውደ ርዕይና ጉባኤውን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያስመዘገበችው ስኬትና የግሉን ዘርፍ ለማበረታታት የሰጠችው ትኩረት አውደ ርዕይና ጉባኤውን እንድታዘጋጅ አስመርጧታል። በዝግጅቱ ላይ የህክምና ግብዓት አምራቾች፣ የፋይናንስ አቅራቢዎች፣ የፈጠራ ባለቤቶች፣ ኢንቨስሮች፣ ተመራማሪዎች እና ከ600 በላይ ተሳታፊዎች እንደሚገኙ ተናግረዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተከትሎ በዘርፉ ለተሰማሩ አምራቾች ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የሚከናወኑ ተግባራት መጠናከራቸውንም ገልጸዋል። ከመሰረት ልማት አቅርቦት አኳያ የህክምና ግብዓቶች የሚመረቱባቸው ልዩ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ዝግጁ መሆናቸውንም እንዲሁ። ከዚህ አኳያም ሶስተኛው የህክምና ግብዓት አምራቾች አውደ ርዕይና ጉባኤ ኢትዮጵያ በዘርፉ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት እና አቅሞችን ለማስተዋወቅ መልካም አጋጣሚ የሚፈጥር ነው ብለዋል።   የህክምና ግብዓት አምራቾች ማህበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ታደሰ ተፈሪ በበኩላቸው፤ አውደ ርዕይና ጉባኤው ለሀገር ውስጥ አምራቾች የገበያ ትስስር ለመፍጠር ዓይነተኛ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶችን ለመሳብና የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማሳለጥ ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። የአፍሪካ ህክምና ግብዓት አምራቾች የንግድ፣ አውደ ርዕይና ጉባኤ ሴክሬታሪያት ሊቀ መንበር እንማሬ ሆሳንግ በኢትዮጵያ ባደረጉት ጉብኝት የሀገር ውስጥ አምራቾችን ለማበረታታት እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ለአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ ሊሆኑ እንደሚችሉ መመልከታቸውን ጠቅሰዋል። አውደ ርዕይና ጉባኤው መሰል ስራዎች እንዲጠናከሩ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠሩም ባሻገር በአፍሪካ ያሉ ባለድርሻ አካላትን በማገናኘት ለዘርፉ ዕድገት ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በኦሮሚያ ክልል የአርብቶ አደሩን ህይወት ለማሻሻል በተሰራው ስራ ውጤት እየተገኘ ነው  
Jan 23, 2026 59
አዲስ አባባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ድርቅን መቋቋም የሚያስችል አቅምን በማጎልበት የአርብቶ አደሩን ህይወት ለማሻሻል በተሰራው ስራ የተሻለ ውጤት እየተገኘ መሆኑን የክልሉ መስኖ ልማትና አርብቶ አደር ቢሮ ገለጸ። የኦሮሚያ ክልል የመስኖና አርብቶ አደር ቢሮ ምክትል ሀላፊ ኢንጂነር አለሙ ረጋሳ እንደተናገሩት፤ የአርብቶ አደሩን ህይወት ለማሻሻል የውሃ አቅርቦትን ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። አርብቶ አደሩ ከእንስሳት እርባታው ጎን ለጎን በግብርና ስራ ላይ በመሳተፍ የምግብ ዋስትናውን ለማረጋገጥ እንዲችል 'ፊና ኦሮሚያ' የተሰኘ ፕሮጀክት ተቀርጾ ሲተገበር ቆይቷል ብለዋል። በ2014 ዓ.ም ከተጀመሩ 73 የፊና ፕሮጀክቶች ውስጥ 37ቱ ግንባታቸው ተጠናቀው አገልግሎት እየሰጡ ሲሆን የተቀሩት ፕሮጀክቶች ደግሞ በግንባታ ላይ ይገኛሉ ብለዋል። በፕሮጀክቱ አነስተኛ እና መካከለኛ የመስኖ ግድቦች በብዛት የተገነቡ ሲሆን አርብቶ አደሩ ግድቦቹን ለእንስሳት መጠጥ ውኃ እና ለግብርና ልማት እየተጠቀመበት መሆኑንም ገልጸዋል። በተጨማሪም አነስተኛ ግድቦቹ ለእንስሳት መኖ ልማትም እየዋሉ በመሆኑ አርብቶ አደሩ ከእንስሳት ሀብት ልማቱ ተጠቃሚ መሆን መጀመሩን ተናግረዋል። ይህ ብቻ ሳይሆን አርብቶ አደሩ በተለያየ ምክንያት በመሰረተ ልማት ዝርጋታ ወደ ኋላ የቀረ መሆኑን አስታውሰው መሰረተ ልማትን የማሟላት ስራም በስፋት መከናወኑን ገልጸዋል። ከመሰረተ ልማቶቹ መካከል መንገድ፣ መብራት፤ የጤና ተቋማትና ትምህርት ቤቶች ማስፋፋት ስራ መሰራቱን ጠቅሰው በዚህም አርብቶ አደሩ ድርቅ የመቋቋም አቅሙን በማሳደግ ምርታማ እንዲሆን እየተደረገ ነው ብለዋል። በቀጣይም አርብቶ አደሩ ድርቅን የመቋቋም አቅሙን በማጎልበት ህይወቱን ለማሻሻል የተጀመረው ስራ እንደሚጠናከርም ገልጸዋል። በቢሮው የኮንትራክተር አስተዳደር ዳይሬክተር ኢንጂነር ተመስገን ሩንዳሳ በበኩላቸው፤ በክልሉ በከርሰ ምድርና ገጸ ምድር ውሃ በአግባቡ በመጠቀም የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በግንባታ ላይ የሚገኙ የመስኖ ግድቦችን ፈጥኖ ለማጠናቀቅም የተጀመረው ስራ ይጠናከራል ብለዋል።
በክልሉ ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ጀምሮ የመጨረስ ባህል እያደገ መጥቷል
Jan 23, 2026 59
ወላይታ ሶዶ/አርባ ምንጫ/ዲላ፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ለፕሮጀክቶች አፈጻጸም በተሰጠ ትኩረት ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ጀምሮ የመጨረስ ባህል እያደገ መጥቷል ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ለክልሉ መንግስት የተለያዩ አገልግሎት መስጫ የሚውሉ ሕንጻዎች ግንባታ በተለያዩ የክልሉ ከተሞች የመሰረት ድንጋይ ተቀምጧል። በክልሉ ወላይታ ሶዶ ከተማ ለሚገነባው የርዕሰ መስተዳድር ጽህፈት ቤት እና የቤተ መንግስት ሕንፃ ግንባታ የመሰረት ድንጋይ ያስቀመጡት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ናቸው። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህን ወቅት እንደገለጹት፤ በክልሉ ለማይሰሩ ፕሮጀክቶች መሰረተ ድንጋይ የማስቀመጥ ታሪክ ተቀይሮ አሁን ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ጀምሮ የመጨረስ ባህል እያደገ መጥቷል። በአሁኑ ወቅት በክልሉ ስድስት ማዕከሎች የሕንጻ ግንባታ ሥራ መጀመሩን ገልጸው፤ ዘመናዊ ሕንጻዎቹ የህዝቡን ባህል፣ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠትና የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ታሳቢ ባደረገ መልኩ እየተገነቡ መሆናቸውን ተናግረዋል።   ግንባታዎቹን የሚያካሂዱት ሥራ ተቋራጮች ሥራውን በተያዘለት የጊዜ ገደብ በማጠናቀቅ የተሰጣቸውን ኃላፊነት በአግባቡ ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበው፣ የክልሉ መንግስትና ህዝብ ለስራው መሳለጥ ተገቢውን ድጋፍና ክትትል ያደርጋሉ ብለዋል። በተመሳሳይ ዜና በአርባ ምንጭ ማዕከል ለሚገነባው ሕንጻ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሥራና ክህሎት ቢሮ ሃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) የመሰረት ድንጋይ አስቀምጥዋል። በዚህ ወቅት አበባየሁ (ዶ/ር) እንዳሉት በክልሉ ለህብረተሰቡ የሚሰጠውን አገልግሎትና የልማት ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።   በክልሉ ፍትሃዊ የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ህዝብን ያሳተፈ ሥራ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። የክልል ቢሮዎች ግንባታቸው ሲጠናቀቅ ለከተማው ተጨማሪ ውበት ከመሆን ባለፈ ህብረተሰቡ የተለያዩ አገልግሎቶችን በቅርበት እና በአንድ ማዕከል እንዲያገኝ ስለሚያስችሉ ወጪና እንግልቱን ያስቀርለታል ብለዋል። በዲላ ከተማ ለሚገነባው የቢሮ ሕንጻ የመሠረት ድንጋይ ሲቀመጥ የተገኙት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት በተለያዩ ከተሞች ግንባታቸው የተጀመረው የቢሮ ሕንጻዎች በተያዘላቸው የጊዜ ገደብና ጥራት እንዲጠናቀቁ ተገቢው ክትትልና ቁጥጥር ይደረጋል።   በከተማው ዛሬ የመሰረት ድንጋይ የተጣለለት ሕንጻ ሲጠናቀቅ ለህብረተሰቡ የሚሰጠውን አገልግሎት በተሻለ በማድረግ ህዝቡን ፍትሀዊ የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል። በተለያዩ ከተሞች ለሚገነቡና በግንባታ ሂደት ላይ ላሉ የቢሮ ሕንጻ ፕርጀክቶች 4 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ መመደቡን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ዲዛይንና ግንባታ ቁጥጥር ድርጅት ምክትል እና የምህንድስና ዘርፍ ኃላፊ ኢንጂነር አክሊሉ ነጋ ናቸው።
የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራውን በትጋት በመወጣት ለሀገራዊ እድገት የሚኖውን ፋይዳ ለማሳካት በትኩረት እንሰራለን
Jan 23, 2026 367
አምቦ፤ጥር 15/2018(ኢዜአ)፡- የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራውን በትጋት በመወጣት ለሀገራዊ እድገት የሚኖውን ፋይዳ ለማሳካት በትኩረት እንደሚሰሩ ሰልጣኞች ገለጹ። በኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት የአምቦ ቅርንጫፍ በ2ኛው ዙር የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ላይ ለሚሰማሩ መረጃ ሰበሳቢዎች እና ተቆጣጣሪዎች ስልጠና ሰጥቷል።   ኢዜአ ያነጋገራቸው ሰልጣኞች ጥራት ያለውን የኢኮኖሚ ድርጅቶች መረጃ በአግባቡ በመሰብስብ ለሀገር እድገት ሚናቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡ ከሰልጣኞች መካከል ኪቢቱ ጋረደው፣ ስልጠናው ጥራት ያለውን መረጃ ከህብረተሰቡ ለመሰብሰብ እንደሚያግዛት ገልጻለች።   ይሄም መንግስት የህብረተሰቡን የልማትና መልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት ለሚያደርገው ጥረት መሰረት እንደሚሆንም ገልጻለች። ሌላው ሰልጣኝ አቶ ፀጋዬ ጌታቸው እንዳሉት፤ የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ መረጃዎቹን በትክክል ለመሰብሰብ ዲጂታል ቴክኖሎጅን እንደሚጠቀም ገልጿል። በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የጥናት፣ ምርምርና ስልጠና ክፍል መሪ ስራ አስፈፃሚ ሶርሴ ጉተማ እንዳሉት፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ 2ኛ ዙር የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ በ55 የስልጠና ማዕከሎች እየተሰጠ ነው።   ቆጠራውን በተደራጀ መልኩ ለመምራት የመንግስት የልማት ድርጅት፣ የግል ኢኮኖሚ ድርጅቶች፤ ባለሃብቶች እና ሌሎች አካላት ትብብር እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል። የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራው የኢኮኖሚ ዘርፉን ሁኔታና የሀገሪቷን ጠቅላላ ሀብት ለማወቅና የፖሊሲ አማራጮችን ለማውጣት እንዲሁም ምርምሮችን ለማካሄድ ማለሙን ተናግረዋል ፡፡   በአገልግሎቱ የአምቦ ስታቲክስ አገልግሎት ቅርንጫፍ ጽህፈትቤት ኃላፊ አቶ አቡና ገደፋ በበኩላቸው፤ እየተሰጠ ያለው ስልጠና መረጃ ሰብሳቢዎች ጥራትና ወቅቱን የጠበቀ መረጃን መሰብሰብ የሚችሉበትን አቅም ለመገንባት ነው ብለዋል። ለዚህም 3 ሺህ 145 መረጃ ሰብሳቢ ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠናውን በመውሰድ በአካባቢው ያሉ የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ላይ ይሰማራሉ ነው ያሉት።      
የኢትዮጵያን የስፖርት ቱሪዝም ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው
Jan 23, 2026 81
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የስፖርት ቱሪዝም ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ገለጸ። የስፖርት ቱሪዝም በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ የመጣ የቱሪዝም ዘርፍ ነው። በኢትዮጵያም በአትሌቲክስ፣ በጎዳና ላይ ሩጫ፣ ባሕላዊ እና ሌሎች የጉብኝት ቦታዎች የእግር ጉዞ የስፖርት አይነቶች ለስፖርት ቱሪዝም ተጠቃሚነት ምቹ አቅሞች ናቸው። የኢትዮጵያ የስፖርት ቱሪዝም አቅሞችም በሀገር ገጽታ ግንባታ፣ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን በማሳደግና በስፖርት መሠረተ ልማት ግንባታ ከፍተኛ ፋይዳ አላቸው። የአዲስ አበባና ሌሎች ዋና ዋና ከተሞች የኮሪደር ልማትም በስፖርት ማዘውተሪያ ስታዲየም ግንባታ፣ በብስክሌትና በእግር መንገድ የስፖርት ዘርፎች ለስፖርት ቱሪዝም ዕድገት ወሳኝ ምዕራፍ ከፍተዋል። በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በጥቂት ዓመታት ውስጥ በአዲስ አበባ የተገነቡ መሠረተ ልማቶች ለስፖርት ቱሪዝም እንቅስቃሴ ምቹ ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል። ‎የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴዔታ መኪዩ መሐመድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አዲስ አበባን ለስፖርት ቱሪዝም ምቹ ለማድረግ የተሰሩ ተግባራት ከፍተኛ ውጤት እያስገኙ ነው ብለዋል። በተለይም የመዲናዋ የኮንፍረንስ ቱሪዝም ማዕከልነት እያደገ መምጣት ለስፖርት ቱሪዝም እንቅስቃሴ ወሳኝ ምዕራፍ መክፈቱን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት ሁለት ዓመታት 16 ዓለም አቀፋዊ የስፖርት ሁነቶችን በስኬት በማስተናገድ ኢትዮጵያ ለስፖርት ቱሪዝም አቅም እንዳላት በተግባር ማሳየት እንደተቻለ ተናግረዋል። ለአብነትም በየዓመቱ በርካታ የሀገር ውስጥና የውጭ ዜጎች የሚሳተፉበት ታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ እና 46ኛው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በስኬት መስተናገዳቸውን አንስተዋል። በኢትዮጵያ በስፖርት ቱሪዝም የሚስተናገዱ ሁነቶችም በሀገር ገጽታ ግንባታና በውጭ ምንዛሬ ገቢ እንዲሁም የስፖርት መሠረተ ልማትን በማስፋፋት አዎንታዊ ሚና እንዳላቸው አብራርተዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያ 32 ብሔራዊ የስፖርት ፌዴሬሽኖች ዓለም አቀፍ የስፖርት ሁነቶችን ወደ ሀገር ውስጥ እንዲያመጡ በትብብር እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ የሚካሄዱትን 5ኛው የአፍሪካ ወጣቶች ኦሎምፒክና የአፍሪካ የባህል ስፖርት ፌስቲቫል ለማስተናገድ በቂ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። የ‎ኢትዮጵያን የስፖርት ዲፕሎማሲ እና ስፖርታዊ ኩነቶች የማስተናገድ አቅም በማሳደግ ቀዳሚ የአፍሪካ የስፖርት ቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
በአዲስ አበባ በአጭር ጊዜ የታየው የልማት ሥራ የሚደነቅ ነው - የአፋሕድ አመራሮች
Jan 23, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ በአጭር ጊዜ ውስጥ የታየው የልማት ሥራ የሚደነቅ ነው ሲሉ የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) አመራሮች ገለጹ፡፡ የአፋሕድ ከፍተኛ አመራሮች ማስረሻ ሰጤ እና ፈንታው ሙሀባውን ጨምሮ የድርጅቱ አባላት በመዲናዋ ያለውን የልማት እንቅስቃሴ በሥፍራው ተገኝተው ጎብኝተዋል። በዚህም በመዲናዋ የተሰሩ የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ ልማት እና የተለያዩ የልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል፡፡ በአዲስ አበባ በአጭር ጊዜ ውስጥ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች እጅግ የሚደነቁ መሆናቸውን መግለጻቸውን ኢቢሲ ዘግቧል።   እየተሰራ ያለው ሥራ ስንሰማው ከነበረው በተቃራኒው አስደናቂ ሆኖ አግኝተነዋል ያሉት የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋሕድ) አመራሮችና አባላት፤ ሥራው ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው ገልፀዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለረጅም ዘመናት በግጭት ውስጥ መቆየቷን ያስታወሱት አመራሮቹ፤ ሰላሟን ለማስጠበቅ እና ልማት ለማረጋገጥ በጋራ መሥራት ይገባል ብለዋል፡፡ በአማራ ክልል መንግሥትና የአማራ ፋኖ ሕዝባዊ ድርጅት (አፋህድ) መካከል የተደረሰውን ዘላቂ የሰላም ስምምነት ውጤታማ የሚያደርግ ስምምነት በትናንትናው ዕለት መፈረሙ ይታወቃል፡፡
በአማራ ክልል 293 ሺህ ሔክታር መሬት በበልግ ወቅት ይለማል
Jan 23, 2026 67
ባሕር ዳር፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በዘንድሮው የበልግ ወቅት 293 ሺህ ሔክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች እንደሚለማ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በልግ አብቃይ በሆኑ የሰሜን ሸዋ፣ ደቡብና ሰሜን ወሎ ዞኖች 293 ሺህ ሔክታር መሬት በማልማት ከ5 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱን በቢሮው የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማንደፍሮ አስላከ (ዶ/ር) ተናግረዋል።   የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግም 4 ሺህ 226 ኩንታል ምርጥ ዘር እና ከ50 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ እንደሚሠራጭ ለኢዜአ ገልጸዋል። አርሶ አደሩም ዝናብን በማሳው ውስጥ ለማስቀረት የውኃ ማስረጊያ ስትራክሮችንና የውኃ ማጠራቀሚያ ጉድጓድ እንዲያዘጋጅ እየተደረገ ነው ብለዋል። አነስተኛ የበልግ ዝናብ ባለባቸው አካባቢዎች ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን ማልማት እንዲቻል እየተሠራ መሆኑንም ጠቁመዋል። የበልግ ዝናብ በአንዳንድ የክልሉ አካባቢዎች መዝነብ መጀመሩን ጠቁመው፤ ከተያዘው ጥር ወር መጨረሻ ጀምሮ የዘር ሥራ እንደሚካሄድ አመላክተዋል።   በደቡብ ወሎ ዞን የደሴ ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደሮች አሕመድ ሙሄ እና የሱፍ ሀሰን እንዳሉት፤ ግማሽ ሔክታር መሬታቸውን በበልግ ወቅት በገብስና በስንዴ ለማልማት የእርሻ ሥራ ጀምረዋል። ምርታማነትን ለማሳደግም ማሳቸውን ደጋግመው በማረስ ለማለስለስና የምርት ማሳደጊያ ግብዓቶችን ለመጠቀም መዘጋጀታቸውን አረጋግጠዋል።
የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ለኢትዮጵያ እና ዛምቢያ አዳዲስ የኢንዱስትሪ እና ንግድ እድሎችን ይዞ መጥቷል - አምባሳደር አልበርት ሙቻንጋ
Jan 23, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦‎ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ኢትዮጵያ እና ዛምቢያ የኢንዱስትሪና ንግድ ትብብራቸውን የበለጠ ማስፋት የሚችሉበትን ሰፊ እድል መፍጠሩን አምባሳደር አልበርት ሙቻንጋ ገለጹ። የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ስምምነት እ.አ.አ በ2018 በሩዋንዳ ርዕሰ መዲና ኪጋሊ በተካሄደው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ልዩ ስብሰባ ላይ 54 የአፍሪካ ሀገራት ፈርመዋል። ስምምነቱን ወደ ስራ ለማስገባት 22 ሀገራት በሀገራቸው ሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ማስፀደቅ ይጠበቅባቸው የነበረ ሲሆን በወቅቱ ኢትዮጵያን ጨምሮ 31 ሀገራት በማጽደቃቸው ስምምነቱ ከታህሳስ 2013 ዓ.ም አንስቶ ተግባራዊ እየሆነ ይገኛል።   አሁን ላይ 48 ሀገራት ስምምነቱን በየሀገሮቻቸው ምክር ቤት አጽድቀዋል። በኢትዮጵያ የዛምቢያ አምባሳደር አልበርት ሙቻንጋ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና 1 ነጥብ 5 ቢሊየን ህዝብ በሚኖርባት አህጉር ነጠላ ገበያን በመፍጠር ሰፊ እድሎችን ይዞ መምጣቱን ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እና ዛምቢያ ስምምነቱን ፈርመው በህግ አውጪ ምክር ቤቶቻቸው ካጸደቁ ሀገራት መካከል እንደሚገኙበትም ጠቅሰዋል። ይህም ሁለቱ ሀገራት በቀላሉ እንዲገበያዩ፣ ኢንዱስትሪዎችን እንዲያስፋፉና ምርቶቻቸውን በአፍሪካ ገበያ እንዲሸጡ መልካም አጋጣሚ መፍጠሩን ተናግረዋል። ሀገራቱ በአህጉራዊው ማዕቀፍ አማካኝነት ከሁለትዮሽ ትብብር ባሻገር ቀጣናዊ ትስስርን እውን ለማድረግ መስራት ይገባቸዋል ነው ያሉት።   እንደ አምባሳደሩ ገለጻ በርካታ የአፍሪካ ሀገራት የሀገር ውስጥ ገበያ ፍላጎትን ለማሟላት ብቻ ሲሰሩ መቆየታቸው አቅማቸው እንዲገደብ አድርጓል። ኢትዮጵያ እና ዛምቢያን ጨምሮ የሌሎች የአፍሪካ ሀገራት የንግድ ማህበረሰቦች ያላቸውን ሀብት በማቀናጀትና በጋራ ማምረት ከቻሉ ከራሳቸው አልፈው ለአፍሪካ ገበያ የሚበቁ ምርቶችን ማቅረብ እንደሚቻል ነው የገለጹት። የአፍሪካ ሀገራት የጋራ የምርት አቅም በመገንባትና የድንበር ተሻጋሪ ንግድን በማጠናከር ለኢኮኖሚ ትስስር እና ለተቀናጀ የጉምሩክ አሰራር ስርዓት እውን መስራት እንዳለባቸውም አመልክተዋል። በተጨማሪም ሀገራት ከአፍሪካ ውጪ የሚገኙ ምርቶች ላይ ተመሳሳይ መጠን ያለው ታክስ በመጣልና በአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ማዕቀፍ በጋራ በመስራት የአፍሪካን ንግድ መጠበቅና ኢኮኖሚያቸውን ማጠናከር እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል። ነጻ የንግድ ቀጣናው ለአፍሪካ ኢንዱስትሪ፣ የኢኮኖሚ እድገት እና እየተቀየረ ባለው የዓለም ስርዓት ውስጥ አፍሪካ ጠንካራ ሚና እንዲኖራት የሚያስችል መሆኑንም ተናግረዋል። የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጠና በያዛቸው ሀገራት ብዛት በዓለም ትልቁ የንግድ ቀጣና የሚያደርገው ሲሆን 54ቱ ሀገራት አሁን ያላቸው አጠቃላይ የምርት መጠን 3 ነጥብ 4 ትሪሊየን ዶላር እንደሆነ መረጃዎች ያሳያሉ።   ነጻ የንግድ ቀጣናው የአፍሪካ ሀገራትን የእርስ በእርስ የንግድ ልውውጥ ከማሳደግ ባለፈ የኤክስፖርት አቅማቸውን በማጎልበት ለኢኮኖሚ እድገታቸው ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው የኢኮኖሚ ባለሙያዎች ይገልጻሉ። የዓለም ባንክ ባስቀመጠው ስሌት የነጻ ንግድ ቀጣናው ስምምነት ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ከሆነ 30 ሚሊየን አፍሪካውያንን ከከፋ ድህነት፤ 70 ሚሊየን የአህጉሪቱ ዜጎችን ደግሞ ከመካከለኛ ድህነት ያወጣል ተብሎ ይጠበቃል። ኢትዮጵያ እና ዛምቢያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን እ.አ.አ በ1965 መጀመራቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመኸር እርሻ ከለማው ሰብል እስከአሁን 37 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ተሰብስቧል
Jan 23, 2026 88
አሶሳ፤ ጥር 15/2018(ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በመኸር እርሻ ከለማው ሰብል እስከአሁን 37 ሚሊዮን ኩንታል ምርት መሰብሰቡን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሰፊ ለም መሬትና በቂ የውሃ አማራጮች ያሉት ቢሆንም ባለው የተፈጥሮ ሀብት ልክ ታርሶ ለህብረተሰቡ ጥቅም ሳይውል ቆይቷል። ከለውጡ ዓመታት ወዲህ ግን አርሶ አደሩ እና ከፊል አርሶ አደሩ ያለውን መሬት በስፋት እንዲያርስ የክልሉ መንግሥት ሰፊ ስራ እየሰራ ይገኛል። በዚህም በተገኘው መነቃቃት ከክልሉ ነዋሪ ባለፈ ባለሀብቶችም በክልሉ በስፋት በግብርና ስራው በመሰማራታቸው ምርትና ምርታማነት እየጨመረ መምጣቱ ተገልጿል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ባበክር ሀሊፋ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በክልሉ ከመኸር እርሻው በተጓዳኝ የበጋ ስንዴ የመስኖ ልማትን ጨምሮ ልዩ ልዩ ሰብሎች በዓመት ሁለትና ሶስት ጊዜ እየተመረተ ይገኛል። በዚህም በክልሉ በመኸር እርሻ ከለማው 1 ነጥብ 6 ሚሊየን ሄክታር ማሳ ላይ በተካሄደው የቅደመ ምርት ጥናት 54 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚገኝ ተገምቷል። እስከአሁን ድረስም ከተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ከ37 ሚሊየን 511 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን አስታውቀዋል። ከተሰበሰበው ምርት ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሚሆነው ከበቆሎ እና ማሽላ ሰብል የተገኘ ምርት እንደሆነም ተናግረዋል። በክልሉ የምርት አሰባሰብ ሂደቱ መቀጠሉን ገልፀው፥ በተለይም ከ137 ሺህ ሄክታር በላይ በማሽላ የለማ ማሳን ጨምሮ ሌሎች የሰብል ዓይነቶች እየተሰበሰቡ በመሆኑ ዕቅዱ እንደሚሳካ አመላክተዋል። የምርት ብክነት እንዳይከሰትም አርሶአደሩ ሰብልን ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ እንዲሰበሰብ መደረጉን ተናግረዋል። አርሶአደሩ የኩታገጠም እርሻ የሚያስገኘውን ዘርፈ ብዙ ጠቃሜታ በመገንዘብ እንዲሁም የግብርና ሜካናይዜሽን በስፋት ማከናወኑን አብራርተዋል። በክልሉ የቅባት እህሎች ምርትም በየጊዜው እየጨመረ መምጣቱን የተናገሩት አቶ ባበክር፤ ከ300 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ የለማ ሰሊጥ እና አኩሪአተር ምርት መሰብሰቡን እና ለኢትዮጵያ ምርት ገበያ መቅረቡን አንስተዋል። አርሶ አደሩ ከመኸር እርሻ በተጨማሪ በመስኖ ልማት አትክልትና ፍራፍሬ በማልማት ውጤታማ የግብርና ስራ እያከናወነ እንደሆነ አክለዋል።      
አዲስ አበባ እያስመዘገበች የምትገኘው ሁለንተናዊ ለውጥ ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት የሚሆን ነው
Jan 22, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ አዲስ አበባ ከተማ እያስመዘገበች የምትገኘው ሁለንተናዊ ለውጥ ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት የሚሆን ነው ሲሉ የተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ከንቲባዎች ገለጹ፡፡ በአዲስ አበባ የልማትና የገቢ አሰባሰብ እንቅስቃሴ ላይ ያላቸውን አድናቆትም ተናግረዋል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ሲካሄድ የቆየው የአሕጉራዊ የተሞክሮ ልውውጥ እና የድርጊት መርሃ-ግብር ግምገማ አውደ ጥናት ተጠናቅቋል። በአውደ ጥናቱ ላይ የተሳተፉ የአፍሪካ ከተሞች ከንቲባዎችና የስራ ኃላፊዎች በአዲስ አበባ ያለውን የልማት እንቅስቃሴና የዲጂታል የገቢ አሰባሰብ ስርዓት ተመልክተዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ከንቲባዎች ጋር በመሆን የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮን የስራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል። በተጨማሪም የአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ከንቲባዎች የከተማዋን የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች ተዘዋውረው ተመልክተዋል። ተሳታፊዎቹ በጉብኝታቸው ወቅት በአዲስ አበባ የታዘቧቸው ተሞክሮዎች ለሀገሮቻቸው ትልቅ ትምህርት የሚሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የታንዛንያ ዳሬሰላም ከተማ ከንቲባ ኑረዲን ቢላለ፤ አዲስ አበባ ከተማ ራሷን በራሷ ለማስተዳደር የምታደርገውን ጥረት አድንቀው፤ ስለ አዲስ አበባ ከተማ አሁን በቂ ግንዛቤ አግኝቻለሁ ብለዋል። ከተማዋ ግብር የምትሰበስብበትንና ተግባራትን የምታከናውንበትን መንገድ መመልከታቸውን ጠቅሰው ከዚህም ሰፊ ልምድ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ ያገኙትን ተሞክሮዎች በዳሬሰላም ተግባራዊ እንደሚያደርጉም ጠቁመዋል፡፡   የሉሳካ ከንቲባ ቺላንዶ ቺታንጋላ አንዲት ከተማ ስኬታማ ለመሆን ጠንካራ የገቢ አሰባሰብ ስርዓት ሊኖራት እንደሚገባ ጠቅሰው፤ በአዲስ አበባ ያየነው የገቢ አሰባሰብ ስርዓትና ገቢ እንዳይባክን የሚደረጉ የፈጠራ ስራዎች የሚደነቁ ናቸው ከዚህም ብዙ ልምድ ቀስመናል ብለዋል።   የካሜሩን ያወንዴ ከተማ የበጀት ቢሮ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አሞዉጎ ብረቲንደ በበኩላቸው፤ በአዲስ አበባ የተመለከቱት የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ድንቅ ነው ሲሉ ገልጸውታል። በተለይም በገቢ አሰባሰብ በኩል የተመለከቱት የቴክኖሎጂ አጠቃቀም በካሜሩን ሊተገበር የሚገባው ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ የከተሞች ትራንስፎርሜሽንን የልማት እቅዷ ማዕከል ማድረጓ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት አርአያ የሚሆን ነው
Jan 22, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የከተሞች ትራንስፎርሜሽንን የልማት እቅዷ ማዕከል ማድረጓ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት አርአያ የሚሆን ነው ሲሉ የቢግ ዊን ፊላንትሮፒ የከተሞች ከፍተኛ ዳይሬክተር ሄስቲንግስ ቺኮኮ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያን የከተሞች የትራንስፎርሜሽን ጉዞ ለማፋጠንና የከተሞችን የሀብት ማሰባሰብ አቅም ማሳደግ የሚያስችል ስልታዊ ስምምነት ተፈረመ። ስምምነቱን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ከዓለም አቀፉ ተቋም ቢግ ዊን ፊላንትሮፒ (Big Win Philanthropy) ጋር በይፋ ተፈራርመዋል።   የቢግ ዊን ፊላንትሮፒ የከተሞች ከፍተኛ ዳይሬክተር ሄስቲንግስ ቺኮኮ በፊርማ ሥነ ስርዓቱ ላይ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የከተሞችን ትራንስፎርሜሽን የልማት እቅዷ ማዕከል ማድረጓ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ትልቅ አርአያነት ያለው ተግባር ነው። ኢትዮጵያ የከተሜነትን ሂደት በታቀደ ስልት እና በጠንካራ ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት እየመራች መሆኑ የሚደነቅ ነው ብለዋል። የአፍሪካ የወደፊት ዕጣ ፈንታ በከተሞች ስኬት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ጠቁመው፤ ከተሞች ለዜጎቻቸው ለሚሰጧቸው አገልግሎቶች ስትራቴጂካዊ ኢንቨስትመንት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ምርታማነትን ማሳደግ፣ ጥራት ያለው መሠረተ ልማት ማቅረብ እንዲሁም ፍትሐዊና ተደራሽ አገልግሎቶችን ማረጋገጥ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ የያዘችው ጠንካራ የለውጥ መርሃ ግብር ውጤታማ እንዲሆን ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥርም ጠቁመዋል፡፡ ይህ አዲስ የተፈረመው ስምምነት የሀብት ማሰባሰብ፣ የፋይናንስ አስተዳደር እንዲሁም የትራንስፎርሜሽን ጉዞውን ማፋጠን በሚሉ ቁልፍ ጉዳዮች ላይ በትኩረት እንደሚሰራ ተመላክቷል፡፡
ኢትዮጵያ የማር ምርታማነትን ለማሳደግ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮች ተግባራዊ እያደረገች ነው
Jan 22, 2026 100
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የማር ምርታማነትን ለማሳደግ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮች ተግባራዊ እያደረገች መሆኑን ተገለጸ። የኢትዮጵያ ንብ ሀብት ማህበር እና የተባበሩት መንግስታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት(UNIDO) በንብ ሀብትና በማር ምርታማነት ዙሪያ የመከሩበት የውይይት መድረክ ተካሂዷል።   በመድረኩ የተገኙት የግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና አሳ ሀብት ዘርፍ የሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ግርማ ሙሉጌታ እንደተናገሩት፤ የማር ሀብትን በውጤታማነት ጥቅም ላይ ማዋል የሚያስችል የተሻሻለ አሰራር ተግባራዊ ተደርጓል። መንግስት ለግብርናው ዘርፍ የሰጠው ልዩ ትኩረት መነቃቃት መፍጠሩን ገልጸው፤ አምራቾች በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራርን እንዲከተሉ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን ጠቁመዋል። ለዚህም ስኬት ከበለጸጉ ሀገራት ጋር የሚደረግ የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር፣ የልምድ ልውውጥ ስራዎች እንዲሁም የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ተሳትፎ ወሳኝ ሚና እንዳላቸው አብራርተዋል። መድረኩ የማር ምርት ጥራትን በመጠበቅ ለውጭ ገበያ የሚቀርበውን ምርት ለማሳደግና ዘላቂ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ያለመ መሆኑም ጠቁመዋል።   በአፍሪካ ህብረት እና በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የተባበሩት መንግስታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት(UNIDO) ተጠሪ ስቴፍን ካግቦ በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ እያስመዘገበች ያለው እድገት የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የግብርና ምርቶችን እሴት ጨምሮ ለማቅረብ የተገነቡት ሶስት የተቀናጁ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ለዘርፉ ትልቅ ተስፋ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። እነዚህ ፓርኮች ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ የፈሰሰባቸውና ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል የፈጠሩ መሆናቸውን ጠቁመው፤ የውጭ ኢንቨስትመንት ፍሰትን በመሳብ በኩል ውጤታማ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም በዘርፉ ስኬታማ ለመሆን ለሚፈልጉ ሌሎች ሀገራት እንደ ትልቅ የልምድ ምንጭ እያገለገሉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ኢትዮጵያ በማር ምርት ዘርፍ የጀመረቻቸው ስራዎች ውጤታማ እንደሚሆኑ ያላቸውን እምነት ገልጸው፤ የUNIDO እና የኢትዮጵያ መንግስት ቅንጅት ለሌሎች ሀገራትም አርአያ የሚሆን ተግባር ነው ብለዋል፡፡   የኢትዮጵያ ንብ ሀብት ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ ነጋሽ በቃና በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ማርን እሴት ጨምሮ ለውጭ ገበያ በማቅረብ በኩል መንግስት ለዘርፉ ምርታማነት ያመቻቸውን የፖሊሲና የአሰራር ድጋፎች በአግባቡ ለመጠቀም ዝግጁ መሆናቸውን አመላክተዋል። ማህበሩ በመንግስትና በግል አጋርነት የሚከናወኑ ተግባራት እንዲጠናከሩ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸው፤ ውይይቱ ለሀገሪቱ የማር ዘርፍ እድገት አዲስ አቅጣጫ ይጠቁማል ነው ያሉት።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም