ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ሕይወትን መለወጥ እንደሚቻል በተግባር እያረጋገጠ ያለው የከተማ ግብርና
Apr 17, 2026 282
የሌማት ትሩፋት አካል በሆነው የከተማ ግብርና በመሰማራት ሕይወትን መለወጥ እንደሚቻል በተግባር እያሳየን ነው ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው በዘርፉ የተሰማሩ የመዲናዋ ነዋሪዎች ገለፁ። የከተማ ግብርና በከተማ ውስጥ በሚገኙ አነስተኛ ቦታዎች፣ መኖሪያ ግቢዎች፣ ጣራዎች ወይም አጥሮች ላይ ቀላል ቁሳቁሶችንና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም አትክልት፣ ፍራፍሬ፣ እንስሳትና ዓሳ በማምረት ህይወታቸውን የሚቀይሩበት የምርት ስርዓት ነው። ይህ ዘርፍ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የኑሮ ውድነትን ከመቀነስ ባለፈ ለሴቶችና ለወጣቶች ሰፊ የስራ ዕድልን በሰፊው የሚፈጥር ነው፤ በመፍጠር ላይም ይገኛል። መንግሥት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ወደ ተግባር የገባው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርም በገጠርም ሆነ በከተማ ዜጎች የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ በማድረግ ረገድ አመርቂ ውጤቶችን በማስመዝገብ ላይ ነው። በአዲስ አበባ በከተማ ግብርና የተሰማሩ ተጠቃሚዎችም በዘርፉ መሰማራታቸው የዕለት ተዕለት የቤት ፍጆታቸውን ከመሸፈን አልፎ አዋጭ የገቢ ምንጭ በመሆን ሕይወታቸውን በተጨባጭ እየቀየረላቸው እንደሚገኝ ነው ለኢዜአ የሚገልጹት። በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ላይ የተሰማራው የወልዳ ወሊኒ ማህበር ሰብሳቢ ተካልኝ ደበሌ በ2014 ዓ.ም መንግሥት ለከተማ ግብርና ስራ የሰጠውን ትኩረት ተከትሎ ማህበራቸው ወደ ከተማ ግብርና ስራ መግባቱን ይገልጻሉ። ማህበሩ በአሁኑ ሰዓት ሰባት አባላት ያሉት መሆኑን በመጠቆም የተለያዩ የአትክልት ምርቶችን በማምረት ለራስ ፍጆታ ከማዋል ባለፈ ለማህበረሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የከተማ ግብርና ስራ በስፋት ያላተለመደ ተግባር እንደነበረ አንስተው፤ አሁን ላይ በግብርና ስራ ላይ የሚሰማሩ ነዋሪዎች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን ያነሳሉ። ሌላኛው በእንስሳት እርባታ ላይ የተሰማራው ወጣት አወቀ አበባው እንደሚለው ዶሮዎችንና የወተት ላሞችን በማርባት ተጠቃሚ በመሆን ላይ ነው። እንቁላል እና የተለያዩ ወተትና የወተት ተዋጽኦ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማህበረሰቡ በማቅረብ ገበያ የማረጋጋት ስራ እየሰሩ መሆኑን ይናገራል። በዘርፉ የተሰማሩት እነዚህ ተጠቃሚዎች፣ በከተማ ግብርና ተሰማርቶ ውጤታማ መሆን እንደሚቻል በተጨባጭ እያረጋገጡ መሆኑን ያስረዳሉ። ሌሎች ዜጎችም መልካም ተሞክሮዎችን በመቀመርና በአካባቢያቸው ያለውን ሀብት በመጠቀም፣ የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የገቢ ምንጫቸውን እንዲያሳድጉ ጥሪ አቅርበዋል። በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የእንስሳትና ሀብትና መኖ ልማት ባለሙያ አሰፉ ሙላቱ እና የሆርቲካልቸር ባለሙያው ማሙሽ አሳምነው እንደሚሉት በመዲናዋ የከተማ ግብርና ስራ ባህል እየሆነ መምጣቱን ይገልጻሉ። በዘርፉ የተሰማሩ አካላት የተሻሻሉ ምርት ዝርያዎችን መጠቀም እንዲችሉ፣ምርትን ሲያመርቱ ደህንነቱን በጠበቀ መልኩ እንዲሆን ሙያዊ እገዛዎችን እያደረጉ እንደሚገኙ ገልጸው፤ ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
በኢትዮጵያ የተስማሚነት ምዘና ድርጅት የሚሰጡ አገልግሎቶችን ዓለም አቀፍ ቅቡልነት የሚያረጋግጥ አቅም እየተፈጠረ ነው
Apr 17, 2026 254
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ የተስማሚነት ምዘና ድርጅት የሚሰጡ የፍተሻ፣ የኢንስፔክሽንና የሰርተፊኬሽን አገልግሎቶችን ዓለም አቀፍ ተቀባይነት የሚያረጋግጥ አቅም እየተገነባ መሆኑን የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መዓዛ አበራ ገለጹ። ኢንጂነር መዓዛ አበራ እንደገለጹት፤ ተቋሙ የሀገሪቱን ምርቶችና አገልግሎቶች የጥራት ደረጃ በማረጋገጥ በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማስቻል እየሰራ ነው። በአሁኑ ወቅትም 124 የላብራቶሪ ፍተሻ ወሰኖች በዕውቅና ሰጭ አካል ኦዲት ተደርጎ ውጤቱ እየተጠበቀ መሆኑን ገልጸዋል። በኢንፔክሽን ዘርፍ በተሰራ ስራም በግብርና ምርት፣ በታሸጉ ምግቦች፣ በኬሚካል፣ በዌር ሀውስና በሊፍት ኢንስፔክሽን 16 ወሰኖችን ማስጠበቅ እንደተቻለ ተናግረዋል። በዘንድሮው ዓመትም በታወር ክሬን፣ በቧንቧ ውሃ ናሙና እንዲሁም በዘይትና በዱቄት ቫይታሚን ማበልጸግ ዘርፎች ተጨማሪ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ለማግኘት ማመልከቻ መቅረቡን ጠቁመዋል። በሰርተፊኬሽን ዘርፍም 47 ነባር የዓለም አቀፍ ዕውቅናዎችን በማስጠበቅ በዘንድሮው ዓመት ብቻ በ16 አዳዲስ ወሰኖች ላይ ዕውቅና ማግኘት መቻሉን አስታውቀዋል። በተጨማሪም 23 ወሰኖችን በመለየት ለዓለም አቀፍ ዕውቅና የሚረዳ የሰነድ ዝግጅትና የአቅም ግንባታ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ አንስተዋል። በዘንድሮ ዓመትም በአሉሚኒየም፣ በቆርቆሮ፣ በሚስማርና በሴራሚክ ምርቶች ላይ አዲስ ዕውቅና መገኘቱን ተናግረዋል። በአካባቢ ጥበቃና በትምህርት አስተዳደር ሥርዓት የተገኘው ዓለም አቀፍ ዕውቅናም ድርጅቱ የሚሰጣቸውን አገልግሎት በማንኛውም ዓለም ተቀባይነት እንዲኖረው የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰዋል። በመጨረሻም ድርጅቱ ግቦችን ለማሳካት ከብሔራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት እንዲሁም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝ አብራርተዋል።
በድሬዳዋ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ልማቱን ለማጠናከር የተጀመረው ጥረት ይጠናከራል
Apr 17, 2026 255
ድሬዳዋ፣ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ በመሰብሰብ፣ የሕዝብን የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች የመፍታት ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ሀርቢ ቡህ ገለጹ። የድሬዳዋ አስተዳደር የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ እና የመጪው በጀት ዓመት የትኩረት መስኮች ላይ ያተኮረ ውይይት ተካሄዷል። አቶ ሀርቢ ቡህ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት የገጠርና የከተማውን ነዋሪ መሠረታዊ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት የተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ ልማቶች አበረታች ናቸው። በተያዘው በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራትም የተቀመጡ የልማት ውጥኖችን በላቀ ደረጃ ዳር ለማድረስ የተከናወኑ ሰው ተኮር የልማት ሥራዎች ስኬታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። እነዚህን አበረታች ውጤቶች ይበልጥ ለማሳደግ፣ የገጠሩን አርሶ እና አርብቶ አደር የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ እንዲሁም ድሬዳዋን የኢንዱስትሪ፣ የኢንቨስትመንት እና የሎጀስቲክስ ማዕከል የማድረግ ጉዞን በውጤት ለመደምደም የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አሳስበዋል። የሚፈለገውን ለውጥና ውጤት ለማስመዝገብም የአስተዳደሩ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች የሚያመነጩትን ገቢ አሟጦ የመሰብሰብ ሥራ በቅንጅት ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በሥራ አፈጻጸም ግምገማው ላይ እንደተመለከተው፤ በዘንድሮው ዘጠኝ ወራት 7 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ፣ የተሰበሰበው 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ወይም የዕቅዱን 80 በመቶ መሆኑን ገልጸዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሙሉካ መሐመድ፤ የተሰበሰበው ገቢ ከታቀደው ዕቅድና ኢኮኖሚው ከሚያመነጨው ሀብት አንጻር አነስተኛ መሆኑን አንስተዋል። የአስተዳደሩን ነዋሪዎች የልማት ጥያቄዎች በተሻለ ደረጃ ለመፍታትና ብልጽግናን ለማረጋገጥ በቀሪዎቹ ሦስት ወራት ገቢን አሟጦ የመሰብሰብ ጉዳይ በትኩረት መሠራት ይኖርበታል ብለዋል። ሌሎች የውይይቱ ተሳታፊዎችም በዘጠኝ ወራቱ በገጠርና በከተማ የተሠሩ ሰው ተኮር ልማቶች የሕዝብን አንገብጋቢ ጥያቄዎች በመፍታት ነዋሪው በልማቱ ላይ የባለቤትነት ተሳትፎውን እንዲያሳድግ ማስቻሉን ጠቁመዋል። በቀሪ የበጀት ወራት የተሻለ ሥራ በመሥራት የሚጠበቀውን ውጤት ለማስመዝገብ በቁርጠኝነት እንደሚተጉም አረጋግጠዋል።
በአማራ ክልል ከመኸር እርሻ ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሰብል ምርት ለማግኘት ወደ ስራ ተገብቷል
Apr 17, 2026 147
ኮምቦልቻ፤ ሚያዚያ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ከመኸር እርሻ ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሰብል ምርት ለማግኘት ወደ ስራ መገባቱን በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የክልሉ ገጠር ዘርፍ አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) ገለፁ። የክልሉ ግብርና ቢሮ የ2018/19 መኸር ምርት ዘመን የሰብል ልማትና ጥበቃ ንቅናቄ መድረክ በኮምቦልቻ ከተማ አካሄዷል። በመድረኩ ላይ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) እንደገለፁት፤ በተሻሻሉ አሰራሮች የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ለገበያ ለማቅረብ በትኩረት እየተሰራ ነው። ተግባሩን በማስቀጠልም በ2018/19 የመኸር ሰብል ልማት 5 ነጥብ 58 ሚሊዮን ሄክታር መሬትን በማልማት ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል። የመኸር ሰብሉን ውጤታማ ለማድረግም ለግብዓትና ለቴክኖሎጂ አቅርቦት ትኩረት በመስጠት ለምግብ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ሰብሎች በስፋት እንደሚመረቱ ተናግረዋል። ለዚህም የአደረጃጀት፣ የኩታ-ገጠም ልማት፣ የቴክኖሎጂ እና ሌሎች ዘመናዊ አሰራሮችን መተግበር እንደሚገባም አመልክተዋል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ በበኩላቸው፣ በቴክኖሎጂና በተሻሻለ አሰራር ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በክልሉ በሰብል ልማት እየተመዘገበ የመጣውን ምርታማነት በማጠናክር በሄክታር 36 ነጥብ 3 ኩንታል ለማድረስ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ለዚህም የግብዓት አቅርቦት፣ የእርሻ ማሳ ዝግጅት፣ የባለሙያ ስልጠናና ሌሎችም ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው ለዘንድሮው የመኸር ሰብል ልማት እየተደረገ ካለው የእርሻ ዝግጅት በተጨማሪ ግብዓት በስፋት እየተሰራጨ ነው ብለዋል። በተሻሻለ አሰራር ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ምርት ለኢንዱስትሪዎችና ለገበያ ለማቅረብ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል። በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን ከ561 ሺህ ሄክታር በላይ መሬትን በማልማት ከ19 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ዝግጅት እየተደረገ ነው ያሉት ደግሞ የሰሜን ሽዋ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ችሮታው አስፋው ናቸው። አሲዳማ መሬትን በማከም፣ በኩታ-ገጠም በማልማት፣ በመስመር በመዝራትና ሌሎችንም የምርት ማሳደጊያ ቴክኖሎጂዎች በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራሮች፣ የግብርና ባለሙያዎችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
መሠረተ ልማት የኢኮኖሚው የደም ሥር እና የብልጽግና መሠረት ነው -ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 17, 2026 512
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ መሠረተ ልማት የኢኮኖሚው የደም ሥር፣ የብልጽግናም መሰረት ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ኢትዮጵያ እየተገነባች ነው በሚል መሪ ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ የተዘጋጀውን የኢትዮጵያ የመሠረተ ልማት እና ኮንስትራክሽን ሳምንት ዛሬ ከፍተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው መሠረተ ልማት ለሀገር ዕድገት ወሳኝ ግብአቶችን በማመላለስ የኢኮኖሚው የደም ሥር እና የብልጽግና መሠረት መሆኑን ገልጸዋል። በዐውደ ርዕዩ የተመለከቱትም ወሳኝ የልማት ተቋማት መሠረተ ልማትን እንደ ሀገር በቅንጅትና በትብብር የመምራት አዲስ የሥራ ባህል እየገነቡ መሆናቸውን አመልክተዋል። ባለፉት ዓመታት ፈጠራን፣ ፍጥነትን እና ጥራትን የጉዞ መርሕ በማድረግ ተጨባጭ ስኬቶች መመዝገባቸውን ነው የገለጹት። የመንገድ ርዝመት በብዙ ኪሎ ሜትሮች ማደጉን፣ የታዳሽ ኃይል የማመንጨት ዐቅም ወደ 10 ሺህ ሜጋ ዋት አካባቢ መድረሱን፣ እንዲሁም በዲጂታል ዘርፍ የሞባይል ተጠቃሚዎች 97 ሚልዮን፣ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ደግሞ 57 ሚልዮን መድረሳቸውን በዝርዝር አቅርበዋል። በአዲስ አበባና በሌሎች ከተሞች የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ከተባበርን የማይቻል የለም የሚለውን መርሕ በተግባር ያሳዩ፣ ፍጥነትና ጥራትን ያስተሣሠሩ ፕሮጀክቶች መሆናቸውንም አክለዋል። የመንግሥትን የልማት ጉዞ ለማጣጣል ለሚሞክሩ አካላት እውነታውንና ፍርዱን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ትተን ሥራችንን እንቀጥላለን ሲሉም ተናግረዋል። ኢትዮጵያን ለማበልጸግና ለመገንባት በየበረሃውና በየተራራው እየፈሰሰ ላለው ላብና ደም ተገቢውን ክብር እንሰጣለን ነው ያሉት በመልዕክታቸው። መንግሥት በመንገድ፣ በኃይል፣ በመስኖ፣ በባቡርና በዲጂታል መሠረተ ልማት ዘርፍ ፈጣንና ፍትሐዊ ልማት ለማረጋገጥ የሚሠራውን ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። አሁን ያለንበት ወቅት የሥራ፣ የውጤት እና የተስፋ ዘመን መሆኑን በመጥቀስ፤ ትናንት የተገነባው ለዛሬ፣ ዛሬ የሚገነባው ደግሞ ለነገው ትውልድ ኩራት እና የብልጽግና ዋስትና መሆኑን አስገንዝበዋል።
የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያሳልጡ መሠረተ ልማቶች በልዩ ትኩረት እየተገነቡ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 17, 2026 319
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያሳልጡ መሠረተ ልማቶች በልዩ ትኩረት እየተገነቡ እንደሚገኝ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ''ኢትዮጵያ ትገነባለች፤ ፈጠራ፣ ፍጥነት እና ጥራት ለመሰረተ ልማት እመርታ'' በሚል መሪ ሀሳብ የኢትዮጵያ የመሠረተ ልማትና ኮንስትራክሽን ሳምንት በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ዛሬ ተከፍቷል። መድረኩን በይፋ የከፈቱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፤ ኢትዮጵያ አሁን ላይ የሥራ፣ የውጤት እና የተስፋ ዘመን ላይ ትገኛለች ብለዋል። የለውጡ መንግሥት የሚከተለው የመደመር ዕሳቤም ካለፈው መልካሙን በማስቀጠል፣ ዛሬን ተግቶ በመስራት ለነገ የሚተርፍ አሻራ ማሳረፍ መሆኑን ገልጸዋል። መሠረተ ልማትን በተቀናጀ መንገድ የመምራት አዲስ ባህል እየተፈጠረ መሆኑን ጠቁመው፤ በከተማና ገጠሩ ኢትዮጵያን ለማበልጸግ ዋጋ ለሚከፍሉ ወገኖች ክብር መስጠት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። መንግሥት የኢትዮጵያን ብልፅግና በፅኑ መሰረት ላይ ለማቆም እና ለማሳለጥ መሰረተ ልማትን በልዩ ትኩረት እያጠናከረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ከልማትና ብልፅግና ጉዟችን ለአፍታም አንዘናጋም ነው ያሉት። በኢትዮጵያ እየታየ ያለው ለውጥ ተሞክሮ የሚወሰድበት መሆኑን ያነሱት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በአንጻሩ ለውጡን የሚያጣጥሉ ወገኖች መኖራቸውን ጠቅሰዋል። ለእነዚህ ወገኖችም እኛ እነሱን ለማስረዳት የምናጠፋው ጊዜ የለም፤ ስራችንን እንቀጥላለን፤ እውነታውንና ፍርዱን ለኢትዮጵያ ህዝብና ለእውነተኛ ፈራጆች እንተዋለን ሲሉ ገልጸዋል። መሠረተ ልማት የኢኮኖሚ ዕድገት የደም ሥር መሆኑን በመግለጽ፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት አስደማሚ ስኬቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል። በመንገድ ሽፋኑም ከ126 ሺህ ኪሎ ሜትር ወደ 182 ሺህ ኪሎ ሜትር ማደጉን፣ በአቪዬሽን ዘርፍም ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብቱ የላቁ ስኬቶች መመዝገባቸውን አስረድተዋል። በታዳሽ ኃይል ልማት፣ በዲጂታል ተደራሽነትና በኮሪደር ልማት ዘርፎችም የኢትዮጵያን የዕድገት ጉዞ የሚያፋጥኑ እመርታዊ ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰዋል። በኮንስትራክሽን ዘርፍ የሚታዩ የጊዜ፣ የጥራትና የወጪ ውስንነቶችን ለመቅረፍ የተወሰዱ የፖሊሲና የሕግ ማዕቀፎችም የዘርፉን ውጤታማነት በማስጠበቅ ስኬት መገኙቱን አብራርተዋል። የመንግሥት ከፕሮጀክት ግንባታ ወደ ሥርዓት ግንባታ የተሸጋገረበት ስልታዊ አቅጣጫም ለሀገራዊ ብልፅግና ጉዞ ስኬት መሠረት መሆኑን ገልጸው፤ ይህ የኮንስትራክሽን ሳምንትም የመደመር መንግሥትን የልማት እይታና ሀገራዊ ራዕይ ያስተሳሰረ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል።
በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ስራ አቁመው የነበሩ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ወደ ስራ ማስገባት ተችሏል
Apr 17, 2026 64
ጎንደር፤ ሚያዚያ 9/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ስራ አቁመው የነበሩ በርካታ አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ፡፡ ''እኛም እንሸምት'' በሚል መሪ ሃሳብ በጎንደር ከተማ ሲካሔድ የቆየው ኢትዮጵያ ታምርት የንቅናቄ መድረክ የማጠቃለያ መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡ የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ተፈራ ታረቀኝ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ አምራች ኢንዱስሪዎች የሚያነሷቸውን ችግሮች በመፍታት ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል። በዚህም ባለፉት 9 ወራት ውስጥ ማምረት ያቆሙና ወደ ማምረት ያልገቡ 137 ከፍተኛና መካከለኛ አምራች ኢንዱስሪዎች ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉን አመልክተዋል። በዚሁ ወቅትም ሶስት ሺህ ለሚጠጉ ባለሀብቶችም የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠቱን ገልጸዋል። ኢንዲስትሪዎቹ መሰረተ ልማቶች እንዲሟሉላቸው በማድረግ ፣የግንባታ ቦታዎችን በፍጥነት በማቅረብና የፋይናንስ ችግሮቻቸውን በመፍታትም ነው ስራ እንዲጀምሩ የተደረገው ብለዋል፡፡ በዚህም ለበርካታ ወገኖች የስራ እድል በመፍጠር ፣ ተኪና ለወጭ ንግድ የሚሆኑ ምርቶችን በማቅረብ በአገሪቱ ኢኮኖሚያዊ እድገት ውስጥ የድርሻቸውን እንደሚወጡም ነው የገለጹት። በክልሉ ከ17ሺ በላይ ባለሀብቶችና ባለ ድርሻ አካላት የተሳተፉበት የኢትዮጵያ ታምርት የንቅናቄ መድረኮች መካሄዳቸውን ጠቁመው መድረኮቹም ችግሮችን ተቀራርቦ ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውንም ጠቅሰዋል። በጎንደር ከተማ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት በሚደረገው ጥረት ውስጥ 5 የኢንዱስትሪ መንደሮች ተቋቁመው ወደ ስራ መግባታቸውን የገለጹት ደግሞ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ናቸው፡፡ ጎንደር ከተማ በአግሮ ፕሮሰሲንግ፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ዘርፍ ለሚሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች ምቹና ተመራጭ መሆኑዋን ገልጸዋል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኃላፊ አቶ ግርማይ ልጃለም በበኩላቸው፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 10 መካከለኛና አንድ ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ ገብተዋል ነው ያሉት። በከተማው በኤክስፖርት ምርት የተሰማሩ 7 አምራች ኢንዱስትሪዎች 17ሺ ቶን ምርት ለውጭ ገበያ በማቅረብ 143 ሚሊዮን ዶላር የውጪ ምንዛሬ ማስገኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ በተኪ ምርት የተሰማሩ 99 አምራች ኢንዱስትሪዎች 38 ሺህ ቶን የሚጠጋ ምርት በማምረት ከ149 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማዳን እንዳስቻሉም አመልክተዋል፡፡ በመድረኩ የተሳተፉ ባለሀብቶች በበኩላቸው ከተማ አስተዳደሩ በግንባታና በመሰረተ ልማት አቅርቦት ረገድ ያደረገላቸው ድጋፍ ፈጥነው ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ እንዳገዛቸው አስረድተዋል፡፡ በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችን ጨምሮ ባለሀብቶች ተሳታፊ ሲሆኑ አምራች ኢንዱስትሪዎች ምርቶቻቸውን ያቀረቡበት ኤግዚቢሽንም ተመርቆ ተከፍቷል፡፡
ስትራቴጂካዊ ፋይዳ ላላቸው ቀጣናዊ ኮሪደሮች የሚደረገው የገንዘብ ድጋፍ ሊጠናከር ይገባል- የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ
Apr 17, 2026 317
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ስትራቴጂካዊ ፋይዳ ላላቸው ቀጣናዊ ኮሪደሮች ፈጣን የፋይናንስ አቅርቦት እንዲመቻች አሳሰቡ። የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብስባ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ነው። 28ኛው የአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ የሚኒስትሮች ስብሰባም ጎን ለጎን ተካሂዷል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ በሚኒስትሮች ስብሰባው ላይ ተሳትፈዋል። ከ130 ሚሊዮን በላይ ሕዝብ ላላትና የንግድ እንቅስቃሴዋ ሙሉ በሙሉ በቀጣናዊ ትስስር ላይ ለተመሰረተ አገር፣ ቀልጣፋ የትራንስፖርት ኮሪደሮች አማራጭ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ ነው ሲሉ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በኢኮኖሚ ኮሪደሮች ላይ የሚደረግ ፈጣን የኢንቨስትመንት ንግድን ለማቀላጠፍ፣ ተወዳዳሪነትን ለማጎልበት እና በቀጣናው የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። እነዚህን ኮሪደሮች ቀጣናዊ ዕድገት፣ ትስስርና ዕድል የሚፈጠርባቸው ዋነኛ ሞተሮች ለማድረግ በጋራ መሥራት እንደሚገባም አሳስበዋል። ለቀጣናዊ ኮሪደሮች የሚደረገው የገንዘብ ድጋፍ እንዲጠናከርም ሚኒስትሩ ጥሪ አቅርበዋል። ስብሰባው ከ9 ሺህ 100 ኪሎ ሜትር በላይ የሚሸፍኑ እና 3 ነጥብ 8 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት የተመደበላቸውን አራት ቅድሚያ የሚሰጣቸው ኮሪደሮች አፈጻጸም ገምግሟል። የልማት አጋሮች ከእ.አ.አ 2019 ጀምሮ ለኮሪደሮቹ ግንባታ የሚውል 2 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ድጋፍ አሰባስበዋል። ምንም እንኳን መሻሻሎች ቢታዩም፣ ቀጣናውን ሙሉ በሙሉ ለማስተሳሰር ወሳኝ በሆኑ የመንገድ ክፍሎች ላይ አሁንም የፋይናንስ ክፍተት መኖሩን ሚኒስትሮቹ አመልክተዋል። ውይይቱ ኢንቨስትመንትን በማሳደግ እና አፈጻጸምን ለማፋጠን በሚያስችሉ አዳዲስ የፋይናንስ አማራጮች ላይ ትኩረት አድርጓል። በስብሰባው ላይ የፋይናንስ ክፍተቶችን በመሙላትና ከፍተኛ ፋይዳ ያላቸውን የኮሪደር ፕሮጀክቶች በማፋጠን የቀጣናውን የኢኮኖሚ አቅም ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር እንደሚገባ የጋራ አቋም መያዙን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
የዘላቂ የዕዳ አስተዳደር የኢኮኖሚ ሪፎርሙ ስትራቴጂካዊ ትኩረት ነው -የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ
Apr 17, 2026 327
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዘላቂ የዕዳ አስተዳደርን የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ አካል አድርጋ እየሰራች እንደምትገኝ የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገለጹ። የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብሰባ በዋሺንግተን ዲሲ መካሄዱን ቀጥሏል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ፣ ከስብሰባው ጎን ለጎን ዓለም አቀፍ የመንግስታት ዕዳ (Global Sovereign Debt) የተመለከተ ስብሰባ ላይ ተሳትፈዋል። ኢትዮጵያ በውይይቱ ወቅት፤ በዕዳ ውስጥ ባሉ አገራት፣ በሁለትዮሽ የመንግሥታት አበዳሪዎች፣ በግል አበዳሪዎች እና በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት መካከል ገንቢና ሁሉን አቀፍ ውይይት እንዲኖር መድረኩ ለሚጫወተው ሚና ያላትን አድናቆት ገልጻለች። ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ኢትዮጵያ በቡድን 20 (G20) የጋራ ማዕቀፍ አማካኝነት እያከናወነችው የሚገኘውን የዕዳ ሽግሽግ (debt restructuring) ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ ገለጻ አድርገዋል። የድርድር ሂደቱ ከአጋሮች ጋር ያለውን ጠንካራ ትብብር የሚያንፀባርቅ ከመሆኑም በላይ፣ መንግሥት የዕዳ ዘላቂነትን ለማረጋገጥና የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋትን ለማስፈን ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል። ሚኒስትሩ በገለጻቸው፤ የዕዳ ሽግሽግ ስምምነቱ ግቡን እንዲመታ የባለድርሻ አካላት የተቀናጀና ፈጣን ድጋፍ አስፈላጊ መሆኑን አሳስበዋል። የሪፎርም ስራዎቿን ለማስቀጠልና ምጣኔ ሀብታዊ መረጋጋትን ለማረጋገጥ፤ ከአበዳሪዎችና ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት የሚጠበቀው ገንቢ ተሳትፎና ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ኢትዮጵያ ጥሪዋን አስተላልፋለች። ኢትዮጵያ የዘላቂ የዕዳ አስተዳደርን የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው አካል አድርጋ እየሰራች መሆኑንና ይህም የፊስካል ዲሲፕሊን፣ የሀገር ውስጥ ሀብት አሰባሰብ እና አካታች ዕድገት ላይ ትኩረት እንደሚያደርግ ገልጻለች። መንግሥት ስልታዊ የሆነ የዕዳ አስተዳደርን በመከተል፣ ከዕዳ ሽግሽግ የሚገኙ ዕድሎችን ለዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትና ለልማት ግቦች ለማዋል ያለውን ጽኑ አቋም በድጋሚ ገልጿል። ኢትዮጵያ በውይይቱ ላይ መሳተፏ በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ግንኙነቶች ያላትን ንቁ ተሳትፎና የዕዳ ተጋላጭነትን በጋራ ለመፍታት ከአለም አቀፍ አጋሮች ጋር ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አስታውቋል።
ኢትዮጵያ እና የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ኮርፖሬሽን ስትራቴጂካዊ አጋርነታቸውን ለማጎልበት ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ
Apr 17, 2026 146
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ኮርፖሬሽን ስትራቴጂካዊ አጋርነታቸውን ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሰሩ አስታወቁ። የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብስባ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ይገኛል። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ከስብሰባው ጎን ለጎን ከአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ኮርፖሬሽን (DFC) ዋና ሥራ አስፈጻሚ ቤን ብላክ ጋር የከፍተኛ ደረጃ ምክክር አደረጉ። ውይይቱ በኢትዮጵያ እና በፋይናንስ ኮርፖሬሽኑ (DFC) መካከል ያለውን ስትራቴጂካዊ አጋርነት ማጠናከር ላይ ያተኮረ ሲሆን፣ በተለይም እንደ ትራንስፖርት እና ማዕድን ባሉ ቅድሚያ በሚሰጣቸው ዘርፎች ትብብርን ማስፋት ላይ የሀሳብ ልውውጥ አድርገዋል። ሁለቱ ወገኖች ዘላቂ እና አካታች እድገትን ለማፋጠን የልማት ፋይናንስ ያለውን ወሳኝ ሚና ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ የኢኮኖሚ እና የንግድ ትብብርን ማጠናከር በሚቻልባቸው መንገዶች ላይም መክረዋል። ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለችውን አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የኢንቨስትመንት ምህዳሩን ለማሻሻል የሚደረጉ ጥረቶችን አብራርተዋል። መንግስት ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ያለውን ቁርጠኝነትም አረጋግጠዋል። የአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ፋይናንስ ኮርፖሬሽን (DFC) ግዙፍ ፕሮጀክቶች በተለይም በመሠረተ ልማት እና በሌሎች ስትራቴጂካዊ ዘርፎች በኢትዮጵያ ያለውን ተሳትፎ ለማሳደግ ያለውን ፍላጎት በድጋሚ ገልጿል። ሁለቱም ወገኖች የፋይናንስ ዕድሎችን ለመጠቀም እና የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ ውጤቶችን ለማምጣት የቀጣይ ትብብር አስፈላጊነትን አጽንኦት ሰጥተውበታል። ሁለቱ ወገኖች ትብብራቸውን ለማጠናከር እና በኢትዮጵያ ውስጥ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን የኢንቨስትመንት ኢኒሼቲቮች ለማሳለጥ የጋራ ቁርጠኝነታቸውን መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
በክልሉ ዘመናዊ የመስኖ አውታሮችን በማስፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው- ቢሮው
Apr 17, 2026 120
ባህር ዳር፤ ሚያዚያ 8/2018( ኢዜአ)፡-ዘመናዊ የመስኖ አውታሮችን ግንባታ በማስፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ገለፀ። በክልሉ ባላፉት ዘጠኝ ወራት አንድ ሺህ 131 ሄክታር መሬት ማልማት ያስቻሉ ዘመናዊ የመስኖ ተቋማት ተገንብተው ለአገልግሎት መብቃታቸው ተገልጿል። በክልሉ በመስኖ መልማት የሚችል ከ2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ያለ ቢሆንም እስካሁን በዘመናዊ መንገድ ወደ ልማት የገባው ከ242 ሺህ ሄከታር የሚበልጥ አይደለም። የቢሮው የመስኖ ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ አየልኝ መሳፍንት ለኢዜአ እንዳሉት፤ የዘመናዊ የመስኖ ተቋማት ግንባታ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። በዚህም አርሶ አደሩን ከልማዳዊ አሰራር በማላቀቅ የዘመናዊ መስኖ ተጠቃሚ እንዲሆን የግንባታ ቦታዎችን በጥናት በመለየት ወደ ስራ ለማስገባት ሰፊ ጥረት እየተደረገ እንደሆነም ነው የገለጹት። ባለፉት ዘጠኝ ወራትም 23 መካከለኛና አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ አንድ ሺህ 131 ሄክታር መሬት ማልማት እንደተቻለ ገልፀዋል። በመስኖ ተቋማቱም ከ3 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለ ጠቅሰው፤ በአሁኑ ወቅትም ከ100 ያላነሱ የመስኖ ተቋማት ግንባታ እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልፀዋል። ለመስኖ ተቋማቱ ግንባታ ለተያዘው ዓመት ብቻ ከ4 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ተመድቦ እየተሰራ ሲሆን በቀሪ ወራትም ሌሎች በግንባታ ሂደት ላይ ያሉ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የዘመናዊ መስኖ መስፋፋት እንደ ሃገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማሳካት ተይዞ እየተከናወነ ያለውን ግብ ውጤታማ ለማድረግ በሚያስችል ሁኔታ እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል። የመስኖ ተቋማቱ ግንባታ ለበርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች የስራ ዕድል በመፍጠርም በኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እያስቻሉ መሆኑንም አንስተዋል። በክልሉ በወንዝ ጠለፋና መሰል ባህላዊ የመስኖ ልማት መንገድ 481 ሺህ ሄክታር መሬት እየለማ እንደሆነም ምክትል ቢሮ ኃላፊው ጨምረው ገልፀዋል።
በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር የክላስተር የፍራፍሬ ልማት ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ተከናወነ
Apr 17, 2026 167
ደዋጨፋ፤ሚያዝያ 9/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደና በአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ የሚመራ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ቡድን በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ደዋ ጨፋ ወረዳ በክላስተር የሚካሄድ የፍራፍሬ ልማት ችግኝ ተከላ አስጀምሯል። ከርዕሳነ መስተዳድሮቹ በተጨማሪ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር)፣ የአማራ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋዬ፣እንዲሁም በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር)ና ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ተገኝተዋል። በተጨማሪም ሌሎች የክልል፣የዞን አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በመርሃ ግብሩ ታድመዋል። በክልሉ የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዋና አስተዳዳሪ አቶ አህመድ አሊ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፣የዞኑ ስነ-ምህዳርና የአየር ንብረት ለፍራፍሬ ልማት ምቹ ነው። ዞኑ በገፅና በከርሰ ምድር ውሃ የታደለ በመሆኑ ያለውን ጸጋ በመጠቀም የኩታ-ገጠም የፍራፍሬ ልማት ስራን በዛሬው እለት በይፋ መጀመሩን ገልጸዋል። ይህም እስካሁን በተበጣጠሰ መልኩ ሲካሔድ የነበረውን የፍራፍሬ ልማት ወደ ኩታ ገጠም በማስፋት ለአገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ታልሞ እየተሰራ መሆኑን ያመላክታል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የአካባቢው አርሶ አደሮችን በማደራጀትና ግንዛቤ በመፍጠር የፍራፍሬ ልማት ስራ አዋጭ መሆኑን ከግንዛቤ አስገብተው ወደ ስራ እንዲገቡ እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል።
በቡና ክላስተር የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ ተግባራት ሊጠናከሩ ይገባል
Apr 17, 2026 154
አረካ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡናን በክላስተር በማልማት የአርሶ አደሮችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመረው ተግባር መጠናከር እንዳለበት የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ ገብረመስቀል ጫላ ተናገሩ። ቡናን በክላስተር ማልማት ላይ ያተኮረ ክልላዊ የቡና ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ዛሬ በወላይታ ዞን ቦሎሶ ሶሬ ወረዳ አቹራ ቀበሌ ተካሂዷል። "የቡና ምርት ዕድገት ለኢኮኖሚያችን" በሚል መሪ ሃሳብ በተካሄደ የችግኝ ተከላ መርሀግብር ላይ የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ እንደገለጹት፤ በመንግስት ትኩረት ከተሰጣቸው ብዝሃ የኢኮኖሚ ዘርፎች መካከል ግብርና አንዱ ነው። ከግብርና ምርቶች መካከል ቡና የአንበሳውን ድርሻ እንደሚይዝ ጠቅሰው፣ ቡናን በክላስተር ለማልማት የተጀመረው ሥራ ልማቱን ከማዘመን ባለፈ የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በእጥፍ ስለሚያሳድገው መጠናከር አለበት ብለዋል። የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በማስፋፋትና የግብርና ስራውን በማዘመን ለምርታማነት መጨመር ሁሉም በተለይ የዘርፉ አመራር መረባረብ አለበት ሲሉም አስገንዝበዋል። ህብረተሰቡ ውሃ ገብ ከሆኑ አካባቢዎች ባህር ዛፍና ያረጁ ቡናዎችን በመንቀልና በመጎንደል የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን በመትከል ተጠቃሚ እንዲሆን የባለሙያዎች ድጋፍ መጠናከር እንዳለበትም አሳስበዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ቡና ላይ መስራት በሀገር ኢኮኖሚ ላይ የሚኖረው አስተዋጽኦ የጎላ በመሆኑ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶታል ብለዋል። ለዚህም ዘንድሮ በክልል አቀፍ ደረጃ ከ40 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኞች እንደሚተከሉ ጠቅሰው፣ በቡና ከሚለማው መሬትም 5 ሺህ ሄክታሩ በኩታ ገጠም እንደሚለማ አመልክተዋል። በክልሉ በባህር ዛፍ የተሸፈኑ ማሳዎችን በተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች የመቀየር ሥራ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶታል ያሉት ኃላፊው ዘንድሮ ከሚተከሉ የቡና ችግኞች መካከል 34 ሚሊዮን የሚሆነው በተያዘው ሚያዚያ ወር የሚተከል ነው ብለዋል። የቡና ልማቱ የአርሶ አደሩን ኑሮ ከማሻሻል ባለፈ ለብዙዎች የሥራ ዕድል እየፈጠረ ነው ያሉት ደግሞ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ሳሙኤል ተሠማ (ረ/ፕሮፌሰር) ናቸው። ይህንን ለማጠናከር ለዘንድሮ የበልግ ወቅት ከ6 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ዝግጅት፣ የጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ፣ የኮምፖስት እና የጥላ ዛፎች ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪ በዞኑ በልዩ ንቅናቄ 2ሺህ 253 ሄክታር የነባር ቡና ማሳ ዕድሳት ሥራ እና ከ2 ሺህ በላይ ሄክታር አዲስ የቡና ማሳ ዝግጅት ተከናውኗል ብለዋል። በዞኑ በተለያዩ ክላስተሮች 1 ሺህ 207 ሄክታር ማሳ ላይ በኩታ ገጠም ቡና ተክሎ ለማልማት ቅድመ ዝግጅት ተደርጎ ወደ ትግበራ መገባቱንም ጠቁመዋል። በዛሬው የተከላ መርሃ ግብር ከተሳተፉት ነዋሪዎች መካከል አቶ ዘለቀ ስኔቦ እና መጋቤ ተስፋዬ ሹኬ፤ ከዚህ ቀደም ቡናን በባህላዊ መንገድ ስለሚያመርቱ ከልማቱ ብዙም ተጠቃሚ እንዳልነበሩ አስታውሰዋል። ከዘርፉ ባለሙያዎች በተሰጣቸው ትምህርት መሰረት የባህር ዛፍ ቦታን በተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች በመተካታቸው የተሻለ ምርት ማግኘት መጀመራቸውን ተናግረዋል። በተለይ ቡናን በክላስተር ማልማት ድካምንና ያለአግባብ ይባክን የነበረን ጊዜ በመቀነስ ተጠቃሚነትን ስለሚያሳድግ አጠናክረው ለማስቀጠል መዘጋጀታቸውን ነው የገለጹት። በቡና ችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ላይ ከክልል ጀምሮ በየደረጃው ያሉ የመንግስት ሥራ ኃላፊዎችና የወረዳው ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
በጎንደር ከተማ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 11 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት ገብተዋል
Apr 17, 2026 96
ጎንደር ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦በጎንደር ከተማ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 11 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት እንዲገቡ ማድረግ መቻሉን የከተማ አስተዳደሩ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ አስታወቀ። በከተማው በ400 ሚሊዮን ብር ወጪ በአንድ ባለሀብት የተገነባ የምግብ ዘይት ማምረቻ ፋብሪካ ተመርቆ ስራ ጀምሯል። የመምሪያው ሃላፊ ግርማይ ልጃለም እንዳሉት፤ በዘንድሮው ዓመት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 20 መካከለኛና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ወደ ምርት ማምረት ለማሸጋገር እየተሰራ ነው። ባለፋት ዘጠኝ ወራት በተደረገ የተቀናጀ ጥረትም 10 መካከለኛና አንድ ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪ ወደ ማምረት እንዲገቡ መደረጉን ገልጸዋል። ወደ ምርት እንዲገቡ የተደረጉት ኢንዱስትሪዎችም በአግሮ ፕሮሰሲንግ፣ በጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ማምረት ላይ የተሰማሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። አምራች ኢንዱስትሪዎቹ ከ500 በላይ ለሚሆኑ ወገኖች የስራ ዕድል በመፍጠር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ማሳደግ ያስቻሉ ሲሆን ከ800 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ እንደሆኑም ገልጸዋል። አምራች ኢንዱስትሪዎቹ ወደ ማምረት መሸጋገራቸውም ገበያን በማረጋጋት፣ ተኪ ምርቶችን በማምረትና የውጭ ምንዛሬን በማስቀረት ኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑንም አመልክተዋል። በከተማው የሰፈነው ሠላም አምራች ኢንዱስትሪዎቹ በሙሉ አቅማቸው ወደ ስራ እንዲገቡ ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ያሉት ደግሞ የከተማው ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ናቸው። የከተማ አስተዳደሩ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች የግንባታ መሬት ከማዘጋጀት ጀምሮ መሠረተ ልማቶችን በማሟላት ፈጥነው ወደ ስራ እንዲገቡ ድጋፍ እያደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዘይት ፋብሪካው ባለቤት አቶ አደራጀው ገብረሚካኤል በበኩላቸው፤ ፋብሪካው በቀን 20 ሺህ ሊትር የምግብ ዘይት የማምረት አቅም እንዳለው ተናግረዋል። ፋብሪካው በቀን 400 ኩንታል አኩሪ አተር በጥሬ እቃነት የሚጠቀም ሲሆን ይህም በግብርና ስራ ለተሰማሩ አርሶ አደሮች አስተማማኝ የገበያ እድል የሚፈጥር ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት ለ30 ወገኖች የስራ እድል መፍጠሩን ጠቅሰው፤ 400 ሚሊዮን ብር ወጪ በማድረግ ከተማ አስተዳደሩ ባመቻቸው 7 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ መገንባቱንም ጠቁመዋል። በስነ ስርዓቱ ላይም የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፍ ተለዋዋጭ ሁኔታዎች የማይበገር የምግብ ስርዓት እየገነባች ነው
Apr 17, 2026 127
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ያሏትን የተፈጥሮ ሀብቶች በሚገባ በማወቅና በማልማት ለዓለም አቀፍ ተለዋዋጭ ሁኔታዎች የማይበገር የምግብ ስርዓት እየገነባች መሆኑን የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ። ላለፉት ጥቂት ዓመታት መንግሥት ተግባራዊ ባደረገው የባለብዙ ዘርፍ የኢኮኖሚ ፖሊሲ ለግብርናው ዘርፍ ልዩ ትኩረት በመስጠቱ፣ ዘርፉ አስደናቂ የምርት እድገትና መዋቅራዊ ሽግግር እያስመዘገበ ይገኛል። በተለይም በበጋ ስንዴ እና በመስኖ ልማት ረገድ በስፋት የተከናወኑት ተግባራት ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቀዳሚ የስንዴ አምራች ሀገር እንድትሆን ያስቻሉ ሲሆን፣ ይህም በምግብ ራስን ለመቻል የሚደረገውን ጥረት በእጅጉ አፋጥኖታል። ይህ ስኬት ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ፣ የኢኮኖሚ ጥንካሬዋን እና የግብርና ምርታማነት አቅሟን በተግባር ያሳየ ሆኗል። የግብርና ሚኒስትሩ አዲሱ አረጋ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የሀገርን የምግብ ሉዓላዊነት በተሟላ መልኩ ለማረጋገጥ የምርትና ምርታማነት እድገት መሰረታዊ ነው። ኢትዮጵያ ቀደም ሲል ስንዴ ከውጭ ገዝታ ለማስገባት ታወጣ የነበረውን ከፍተኛ ወጪ ማስቀረት መቻሏን ገልጸዋል። መንግሥት የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና ምርትን ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት፣ በግዥ ከውጭ ይገባ የነበረውን ስንዴ ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ ምርት መተካት እንደተቻለ ሚኒስትሩ አስታውቀዋል። ይህ ታሪካዊ ስኬት የሀገሪቷን የውጭ ምንዛሬ ከመታደጉ ባለፈ ራስን በምግብ ለመቻል ለተያዘው ብሄራዊ ግብ ትልቅ እርምጃ መሆኑን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በምርምር፣ በግብርና ግብዓቶች አቅርቦት እና በተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም ረገድ ሰፊ ስራዎችን በማከናወን ላይ ትገኛለች ብለዋል። በተለይም የማዳበሪያ አቅርቦትን በዘላቂነት ለመፍታት የተጀመረው የፋብሪካ ግንባታ ተጠናቆ ወደ ስራ ሲገባ ከፍተኛ የኢኮኖሚ እና የምርታማነት ለውጥ እንደሚያመጣ ገልጸዋል። ምርታማነታቸው ከፍተኛ የሆነና በሽታን የመቋቋም አቅም ያላቸው ምርጥ ዘሮች በራስ የምርምር አቅም ማውጣት የሚያስችል የግብርና ምርምር ስርዓት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ያላትን የመሬት፣የውሃ እና የሰው ሃይል አቅም በማቀናጀት ለግብርናው ዘርፍ የሚያስፈልጉ የሃይል እና የቴክኖሎጂ ግብዓቶችን ለማሟላት የምታደርገው ጥረት በጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝም ነው ያስገነዘቡት። አንድ ሀገር በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚከሰቱ የጂኦፖለቲካ ለውጦች በነዳጅ አቅርቦትና በምግብ ሉዓላዊነት ላይ የሚያስከትሉትን ብርቱ ተጽዕኖ ለመቋቋም የሚያስችል ስራ በትኩረት መከናወን እንዳለበት አንስተዋል። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ ያላትን የተፈጥሮ ፀጋዎች በሚገባ ለይታ በማወቅና በማልማት፣ ማንኛውንም ወቅታዊ ዓለም አቀፍ ቀውስ መቋቋም የምትችል ጠንካራ ሀገር ለመገንባት በከፍተኛ ቁርጠኝነት እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ይህም ከውጭ የሚመጡ ተጽዕኖዎችን ተቋቁማ የምግብ ሉዓላዊነቷን በተገቢው መንገድ እንድታረጋግጥ የሚያስችላት መሆኑንም ገልጸዋል። የምግብ ሉዓላዊነቷን ያረጋገጠች ጠንካራ ሀገርን ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ በሚደረገው ጥረት አርሶና አርብቶ አደሮች ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛሉም ብለዋል።
በአፋር ክልል የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት እንዳይስተጓጎል በግብረ-ኃይል የታገዘ ቁጥጥር እየተደረገ ነው
Apr 17, 2026 105
ሰመራ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ላይ መስተጓጎል እንዳይፈጠር በክልሉ ርዕሰ መስተዳድር የሚመራ ግብረ-ኃይል ተቋቁሞ ክትትልና ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን የክልሉ መንገድ ልማትና ትራንስፖርት ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ የመንገድ ልማትና ትራንስፖርት ቢሮ የትራንስፖርት ዘርፍ ኃላፊ ወይዘሮ መዲና ማህሙድ እንደገለጹት፤ በክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አወል አርባ የሚመራውና የተለያዩ ተቋማትን ያቀፈው ግብረ-ኃይል፣ ህብረተሰቡ የትራንስፖርት አገልግሎትን ያለ እንግልት እንዲያገኝ እየሰራ ይገኛል። በተለይም ስትራቴጂካዊ በሆነው የኢትዮ-ጅቡቲ መስመር ላይ ለሚንቀሳቀሱ የትራንስፖርት ተጠቃሚዎች ቅድሚያ በመስጠት አገልግሎት እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ኃላፊዋ አክለውም ዘርፉ ከተለያዩ መስኮች ጋር ትስስር ያለው በመሆኑ፣ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ከማህበራትና ከባለድርሻ አካላት ጋር እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በቢሮው የመንገድ ደህንነትና መድን ፈንድ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ሁሴን ቦልኮ በበኩላቸው፤ ግብረ-ኃይሉ በየደረጃው ያሉ ባለድርሻ አካላት ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ አቅጣጫ አስቀምጧል ብለዋል። በዚህም መሰረት ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይትን ከመቆጣጠር ባለፈ፣ ከተፈቀደው በላይ ተጨማሪ የነዳጅ ማጠራቀሚያ ታንከር ይዘው በሚገኙ አካላት ላይ ጥብቅ ክትትል እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። በሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያ የትራፊክ ዲቪዥን ኃላፊ ዋና ሳጅን መሐመድ አህመድ፤ በማደያዎች አካባቢ የሚታየውን የወረፋ መጨናነቅ ለመቀነስና ሊከሰቱ የሚችሉ የትራፊክ አደጋዎችን ለመከላከል ፖሊስ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።
የአርባ ምንጭ ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋ ያላትን ውበት ይበልጥ በማጉላት ለጉብኝት የበለጠ ተመራጭ ያደርጋታል
Apr 17, 2026 167
አርባ ምንጭ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦የአርባ ምንጭ ከተማ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት ከተማዋ ያላትን ውበት ይበልጥ በማጉላት ለጉብኝት የበለጠ ተመራጭ እንደሚያደርጋት ተመለከተ፡፡ በከተማዋ ከ20 ኪሎ ሜትር በላይ የሚሸፍን የተቀናጀ የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ ነው። አርባ ምንጭ ከተማን ለኑሮ፣ ለሥራ፣ ለጉብኝትና መዝናናት የሚመርጧት አስተማማኝ የኢኮኖሚ ኮሪደር፣ ምቹና የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የተለያዩ የልማት ስራዎች በመከናወን ላይ ናቸው። የከተማዋ ከንቲባ መስፍን መንዛ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በከተማዋ ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንና ከነዚህ ውስጥም ከ20 ኪሎ ሜትር በላይ የሚሸፍነው የኮሪደር ልማት አንዱ መሆኑን ተናግረዋል። ልማቱ ከተማዋ ያላትን ውበት ይበልጥ ከማጉላት ባለፈ ክፍለ ከተሞችን እርስ በርስ የሚያገናኝና ከተለያዩ የቱሪዝም መስህብ ሥፍራዎች ጋር የሚያስተሳስር እንደሆነም ተናግረዋል። ፕሮጀክቱ የመንገድ ዳር ማረፊያዎች፣ ፐብሊክ ፕላዛዎች፣ የእግረኛ መንገድ፣ የአይነ ስውራንና የአካል ጉዳተኛ መተላለፊያ፣ የብስክሌት መንቀሳቀሻ፣ የስፖርት ማዘውተሪያ፣ የመዝናኛ ስፍራና የንግድ ቦታዎችን ባካተተ መልኩ እየተገነባ መሆኑንም ከንቲባው አስረድተዋል። እንደ ከንቲባ መስፍን (ዶ/ር) ገለጻ የኮሪደር ልማቱ የአካባቢውን ሕዝብ ባህል፣ እሴትና የተፈጥሮ ፀጋ ታሳቢ ባደረገ መልኩ እየተከናወነ ነው። የኮሪደር ልማቱ ስራ በአሁኑ ወቅት 50 በመቶ ላይ እንደደረሰና ዋና ዋና ሥራዎች እንደተጠናቀቁ ገልጸው፣ አጠቃላይ ስራውን እስከ በጀት ዓመቱ መጨረሻ ለማጠናቀቅ 24 ሰዓት ያለማቋረጥ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ግንባታው ሲጠናቀቅ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለኑሮ፣ ለቱሪዝምና ለሥራ ይበልጥ ምቹ እንድትሆን ያደርጋታል ብለዋል። የከተማው ነዋሪዎች ወደመንገድ የወጡ አጥሮችና ቤቶችን በማንሳት እንዲሁም በልማቱ እየተሳተፉ ያሉ ሠራተኞችን በማበረታታት እያደረጉት ላለው ትብብርም ከንቲባው አመስግነዋል። የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ትዕግስት ባዩ፤ የኮሪደር ልማት ሥራው የከተማዋን ውበት ይበልጥ ከማድመቅ ባለፈ ለበርካቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም ከመንገድ ጥበት የተነሳ ከተሽከርካሪ ጋር እየተጋፋን ስንጓዝ ነበር ያሉት አስተያየት ሰጪዋ፣ በአሁኑ ወቅት የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገድ በመለየቱ በነጻነት ለመንቀሳቀስ እንደቻሉና የተሽከርካሪ አደጋም እየቀነሰ መምጣቱን ገልጸዋል። በየአካባቢው የማረፊያና የመዝናኛ ስፍራዎች መዘጋጀታቸው የደከመ ሰውነትን ለማሳረፍ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር ባለፈ መንገዱ ለእግር ጉዞ ምቹ መሆኑ ጤናን ለመጠበቅ እንደሚያስችልም አመልክተዋል። በከተማዋ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የከተማዋን ደረጃ ከፍ ከማድረግ በላይ አኗኗራችንን ለማዘመን አግዞናል ያሉት ደግሞ አቶ ታጠቅ ሌሎ ናቸው። በከተማዋ እየታየ ባለው የልማት ውጤት መደሰታቸውን ገልጸው፣ የኮሪደር ልማት ሥራ ተጠቃሚነትን እያረጋገጠ መሆኑ የህዝቡ ተሳትፎና ድጋፍ እንዲጠናከር ማድረጉን ተናግረዋል። ነዋሪዎቹ የኮሪደር ልማቱ ስኬታማ እንዲሆን ከአስተዳደሩ ጎን በመቆም እያደረጉት ያለውን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል።
የአፕል ልማት ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ፈጥሮልናል-የጌዴኦ ዞን አርሶ አደሮች
Apr 17, 2026 89
ዲላ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ የአፕል ልማት ለአካባቢያቸው ስነ-ምህዳር ተስማሚ ከመሆን ባለፈ ተጨማሪ ገቢ እያገኙበት መሆኑን በጌዴኦ ዞን የቡሌና የጮርሶ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የአፕል ልማትን በማስፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በ72 ሄክታር መሬት ላይ ከ45 ሺህ በላይ ችግኞች ተከላ እየተከናወነ መሆኑም ተመላክቷል። አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በአካባቢው ባለው የመሬት ተዳፋትነት ምክንያት የአፈር መሸርሸር እንዳያጋጥምና ለምነቱን በመጨመር ረገድ የአፕል ዛፍ የራሱን ሚና እየተጫወተ ነው። በዚህም ዛፉ የአካባቢያቸውን ስነ-ምህዳር በመጠበቅ ከቋሚና ዓመታዊ ሰብሎች በተጨማሪ ገቢ እያስገኘላቸው መሆኑን ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡ አርሶ አደሮች መካከል በዞኑ የቡሌ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሽፈራው መንገሻ ፤ከመንግስት ባገኙት የሙያና የችግኝ ድጋፍ ከዛሬ አምስት ዓመት በፊት ወደ አፕል ልማት መግባታቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በአምስት ዓይነት የተለያዩ ዝርያዎች ከ50 በላይ የአፕል ዛፎች ምርት እየሰጡ እንደሚገኙ አንስተው ምርቱ ከቤተሰብ ፍጆታ አልፎ በዓመት ከአንዱ የአፕል እግር ከ2 ኩንታል በላይ ምርት ለገበያ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ከ200 ሺህ ብር በላይ ተጨማሪ ገቢ እያገኙ እንደሚገኙ ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት ተጨማሪ ችግኞችን በመትከል ተጠቃሚነታቸውን ለማስፋት እየጣሩ መሆኑን ገልጸዋል። በሰብል ማሳቸው ዙሪያ ያለሟቸው የአፕል ችግኞች ለምርት ደርሰው ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንደፈጠሩ ያነሱት ደግሞ የቡሌ ወረዳ አርሶ አደር አብርሃም ሃይሉ ናቸው። እንደ አርሶ አደሩ ገለጻ የአፕል ዛፍ ተዳፋት የሆነውን መሬት በጎርፍ እንዳይጠረግ በማድረግ ለምነቱ እንዲሻሻል እያገዘ ነው። በአሁኑ ወቅት ከ100 በላይ የአፕል ችግኞችን ከዲላ ዩኒቨርሲቲ የችግኝ ጣቢያ በመውሰድ ተከላ እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። የጮርሶ ወረዳ አርሶ አደር አየለ ጅግሶ በበኩላቸው፤ በጓሯቸው ከተከሉት አፕል በሚያገኙት ገቢ ልጆቻቸውን እያስተማሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። የአፕል ልማት ከሚያስገኘው ተጨማሪ ገቢ ባለፈ ለአካባቢው ሥነ ምህዳር ተስማሚ በመሆኑ ልማቱን ለማስፋት ችግኝ እየተከሉ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ አራት ደጋማ ወረዳዎች በ334 ሄክታር መሬት ላይ አፕል እየለማ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የጌዴኦ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትልና የእርሻ ዘርፍ ኃላፊ አቶ በድሉ አየለ ናቸው። ከዚህም በዓመት ከ30 ሺህ 200 ኩንታል በላይ ምርት ለገበያ በማቅረብ አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። ልማቱን በማስፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግም በተያዘው ዓመት በ72 ሄክታር መሬት ላይ ከ45 ሺህ በላይ የተሻሻሉ የአፕል ዝርያዎችን በመጠቀም የልማት ስራው እየተከናወነ መሆኑንም አክለዋል። በተለይም በዘርፉ ወጣቶችን አደራጅቶ ወደ ልማቱ በማስገባት ሃብት እንዲያመነጩ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል።
የጋራ መኖሪያ ቤቶችን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተደራሽነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
Apr 17, 2026 64
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ) ፦ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተደራሽነት ለማሳደግ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስታወቀ። አገልግሎቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ እንዳመለከተው በኮዬ ፈጬ ኮንዶሚኒየም በተለያዩ ሳይቶች የሚገኙ ነዋሪዎችን በተናጠል የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል። በኮዬ ፈጬ ኮንዶሚንየም ፕሮጀክት 11 እና 17 የሚኖሩ ከ12 ሺህ በላይ ነዋሪዎች በየብሎኩ በተገጠመ ባለ ሦስት ፌዝ ቆጣሪ በጋራ ይጠቀሙ እንደነበር አስታውሶ፤ በዚህም በኃይል ማነስና መቆራረጥ ሲቸገሩ ቆይተዋል ብሏል፡፡ አሁን ግን በተናጠል ቆጣሪ እንዲገጠምላቸው በመደረጉ በቂ ኃይል እንዲያገኙ ማድረግ ተችሏል ተብሏል በመረጃው፡፡ ነዋሪዎቹን የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ ለማድረግም 17 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትር የዝቅተኛ ቮልቴጅ መስመር፣ የ8 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የመካከለኛ ቮልቴጅ የመሬት ውስጥ ተቀባሪ መስመርና የ4 ነጥብ 1 ኪሎ ሜትር የመካከለኛ ቮልቴጅ የአየር ላይ መስመር ዝርጋታ መከናወኑ ተገልጿል። በዚህም 53 ትራንስፎርመሮች መተከላቸውንና ለነዋሪዎቹ 12 ሺህ 100 ቆጣሪዎች መገጠማቸውንም አረጋግጧል። በቀጣይ በአዲስ አበባ ቤቶች በኩል የሚፈፀሙ ክፍያዎች እንደተጠናቀቁ በኮዬ ፈጬ ኮንዶሚኒየም በተለያዩ ሳይቶች የሚገኙ ነዋሪዎችን በተናጠል የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ የማድረግ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አመላክቷል። አገልግሎቱ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን የኤሌክትሪክ ተደራሽነት ለማሳደግ ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት እየሰራ እንደሚገኝም አስታውቋል።
በኦሮሚያ ክልል በበልግ አዝመራ እስካሁን ከ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Apr 17, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በበልግ እርሻ እስካሁን ከ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ምርጥ ዘሮች መሸፈኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የሰብል ልማት ዳይሬክተር አቶ ሙስጠፋ ሁሴን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አርሶ አደሩ በበልግ አዝመራው ውጤታማ እንዲሆን ሙያዊ ድጋፍ እና የግብዓት አቅርቦት በአግባቡ ቀርቧል። በአሁኑ ወቅትም የበልግ አብቃይ አካባቢዎች የአንደኛና ሁለተኛ ዙር የማሳ ዝግጅት ተጠናቆ በዘር መሸፈን ስራ በስፋት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። የበልግ አዝመራው እየተካሄደባቸው ከሚገኙ ዞኖች መካከል ምስራቅ ቦረና፣ ጉጂ፣ አርሲ፣ ምስራቅ እና ምዕራብ ሀረርጌ፣ ምስራቅ ባሌ እና ምስራቅ ሸዋ ዞኖች ይገኙበታል ብለዋል። በተለይ በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጡና ለመኽር አዝመራ መሬት የሚለቁ እንደ በቆሎ፣ ጤፍ፣ የቢራ ገብስ፣ ቦሎቄ፣ ስንዴ፣ ማሽላ፣ ማሾና ሌሎች የሰብል አይነቶች መልማታቸውን አንስተዋል። በክልሉ በበልግ እርሻ 1 ነጥብ 9 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በማልማት ከ46 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱንም አስታውሰዋል። በእስካሁኑ እንቅስቃሴ ከ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የአገዳ፣ የብርዕና የጥራጥሬ ሰብሎች መሸፈኑን ተናግረዋል። በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥ 400 ሺህ ሄክታር መሬት በስንዴ ሰብል በኩታ ገጠም መልማቱን ጠቅሰው አጠቃላይ የበልግ እርሻው ስራ 87 በመቶ መድረሱን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። የቀሩት አካባቢዎችም በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚጠናቀቁ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዘንድሮ በልግ እርሻ የዝናብ ሁኔት አመቺ በመሆኑ ከልማቱ በቂ ምርት የሚጠበቅ ነው ብለዋል። ለበልጉ ልማት ከተሰራጨው 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ እስካሁን 366 ሺህ ኩንታል ጥቅም ላይ መዋሉን ተናግረዋል።