ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በክልሉ ለአምራች ኢንዱስትሪው በተሰጠ ትኩረት በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶች ቁጥር እያደገ መጥቷል - አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደ
May 21, 2026 91
ሀዋሳ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፡-በሲዳማ ክልል ለአምራች ኢንዱስትሪው በተሰጠ ትኩረት በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶች ቁጥር እያደገ መምጣቱን የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደ ገለጹ። በሀዋሳ ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ ዛሬ ተመርቋል። የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ በምረቃ ሥነስርዓቱ ላይ እንዳሉት እንደ ሀገር በተፈጠረው ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ በአምራች ዘርፉ ከፍተኛ መነቃቃት ታይቷል። ለአምራች ኢንዱስትሪው በተሰጠው ልዩ ትኩረትም በክልሉ በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶች ቁጥር እያደገ መምጣቱ ተናግረዋል። አምራች ዘርፉ ከፍተኛ የሰው ሃይል የሚፈልግ በመሆኑ የሥራ ዕድል በመፍጠር በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም አፈ ጉባኤዋ ጠቁመዋል። ከአነስተኛ ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪ ማደግ እንደሚቻል አበባ ጨርቃ ጨርቅና ቆዳ ስፌት አክሲዮን ማህበር ያስገነባው የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ አንድ ማሳያ ነው ብለዋል። የክልሉ አንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ አሻግሬ ጀምበሩ በበኩላቸው መንግስት አምራች ኢንዱስትሪውን በማበረታታት በርካቶችን ወደ ሥራ እንዲገቡ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ በክልሉ የተለያዩ ባለሀብቶች በአምራች ኢንዱስትሪው መስክ እንዲሰማሩ ለማበረታታትም በዘርፉ ለሚሰማሩ መሰረተ ልማት የተሟላላቸው ምቹ ቦታዎችን ማዘጋጀቱንም ተናግረዋል። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሀላፊ አቶ አገና ኔቶ እንዳሉት በከተማዋ ከ1 ሺህ በላይ አነስተኛ፣ መካከለኛ እና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ይገኛሉ። ኢንዱስትሪዎቹ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን የሚተኩና ለውጪ ገበያ የሚቀርቡትን በማምረት በኢኮኖሚው ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆናቸውንም አስታውቀዋል። የአበባ ጨርቃ ጨርቅና ቆዳ ስፌት አክሲዮን ማህበር ሥራ አስኪያጅ ወሌ አበጋዝ (ዶ/ር) በበኩላቸው ለፋብሪካው ግንባታ ከ582 ሚሊዮን በር በላይ ወጪ መደረጉን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት ፋብሪካው ለ153 ሰዎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ እድል መፍጠሩን ገልጸው፣ በሙሉ አቅሙ ወደ ሥራ ሲገባ ለ310 ሰዎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በመታገዝ ወደ ኤክስፖርት ምርት መሸጋገራቸውን ጠቁመው፣ ጥራት ያለው ምርት ለማምረትም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በትብብር እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በፋብሪካው የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ወጣት ኤደን ዘርፉ እንዳለችው በፋሽን ዲዛይን ትምህርት መስክ ተመርቃ በፋብሪካው መቀጠሯን ተናግራለች።
በክልሉ በግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ወጣቶችን በሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ ላይ የተጀመሩ ተግባራት ይጠናከራሉ
May 21, 2026 60
ሀዋሳ፤ ግንቦት 13/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ወጣቶችን በሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ ላይ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ገለፀ፡፡ በሲዳማ ክልል የእርሻውን ዘርፍ ለማዘመንና ሜካናይዜሽንን ለማስፋፋት በማለም የእርሻ ትራክተሮችን በዘርፉ ለተደራጁ ወጣቶች የማስረከብ መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡ በዚህ ወቅት የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ መምሩ ሞኬ እንዳሉት፤ በክልሉ እየተከናወኑ ባሉ የግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ሥራዎች ወጣቶችን በሥራ ዕድል ተጠቃሚ የማድረግ ተግባር እየተከናወነ ይገኛል። የግብርና እና ገጠር ትራንፎርሜሽንን ለማረጋገጥ ግቦች ተጥለው ማሳካት የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም የምግብና ሥነ ምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ፣ ለገበያ የማምረት፣ ኤክስፖርትን የማሳደግና ገቢ ምርትን የመተካት እንዲሁም ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ የግብርና ምርቶችን በስፋት የማምረት ግቦች እንዳሉ ጠቅሰዋል፡፡ በግብርና ዘርፍ ለተደራጁ ወጣቶች የእርሻ ትራክተሮች ርክክብ መከናወኑን ገልፀው በዚህም በአጠቃላይ 148 ወጣቶች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አስረድተዋል፡፡ የአካታችና ዘላቂ የግብርና እሴት ሰንሰለት ልማት ፕሮጀክት ብሔራዊ አስተባባሪ ሰለሞን ዳኜ በበኩላቸው ፕሮጀክቱ በገጠር በተለይ ወጣቶችና ሴቶችን አደራጅቶ ተሳታፊ በማድረግ የገጠሩን ኢኮኖሚ የማሳደግ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በመሆኑም ምርትና ምርታማነትን በማስፋትና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በመተካት በኩል ፕሮጀክቱ የተጣለበትን ኃላፊነት ለመወጣት በትኩረት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ትራክተሮቹን ከተረከቡ ማህበራት መካከል የቦና ወረዳ ወጣት ንግስት አምሳለ ማህበራቸው በቆሎ፣ ስንዴ እንዲሁም አቮካዶ፣ ማንጎና ሌሎች የተለያዩ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ፍራፍሬዎችን እንደሚያመርት ገልፃለች፡፡ ከዚህ ቀደም የግብርና ሥራውን ባህላዊ በሆነ መንገድ ስለሚያከናውኑ ውጤታማነታቸው እምብዛም እንደነበር ገልፃ አሁን ላይ ሰፊ መሬትን በትራክተር በተሻለ ሁኔታ በማረስ ተጠቃሚ የሚያደርጋቸውን ዕድል እንዳገኙ ተናግራለች፡፡ የዳራ ወረዳ ወጣት አዲሱ ሌላሞ በበኩሉ ማህበራቸውም ሆነ በአካባቢያቸው ያሉ አርሶ አደሮች በበሬ አልያም በጉልበት የእርሻ ሥራቸውን እንደሚያከናውኑ ተናግሯል፡፡ ትራክተሮቹን የራሳቸውን እንዲሁም በአካባቢያቸው ያሉ አርሶ አደሮችን ማሳ ለማረስ እንደሚጠቀሙባቸው ገልጿል፡፡
የኢትዮጵያን ዕድገትና ብልፅግና በልጆቿ ጥረት ዕውን ማድረግ እንደሚቻል የገላን ኢንዱስትሪ ፓርክ ህያው ምስክር ነው
May 21, 2026 72
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ዕድገትና ብልፅግና በልጆቿ ጥረት ዕውን ማድረግ እንደሚቻል የገላን ኢንዱስትሪ ፓርክ ህያው ምስክር መሆኑን የኢንዱስትሪ ፓርኩን የጎበኙ የመዲናዋ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ግንቦት 8 ቀን 2018 የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክን መርቀው ሥራ ማስጀመራቸው ይታወቃል። ከአዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ አካባቢዎች የተውጣጡ የማህበረሰብ ክፍሎችም የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ የልማት ውጤትና የአምራቾችን የሥራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል። በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት የተጠሪ ተቋማት ዘርፍ ኃላፊ ዳዲ ወዳጆ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ የኢንዱስትሪ ክላስተር መሆኑን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኩም የአምራቾችን ዓለም አቀፍ የተወዳዳሪነት አቅም በመገንባት ሀገራዊ ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት ገንቢ ሚና እንዳለው ተናግረዋል። ለዚህም ፓርኩ የአዲስ አበባና የኢትዮጵያን የብልፅግና ጉዞ የሚያፋጥን የኢንዱስትሪ ምርታማነትን ምኅዳር እንደፈጠረ አንስተዋል። አዲስ አበባ በሁሉም ዘርፍ ስኬታማና ውጤታማ የልማት ሥራዎችን ዕውን የምታደርግ ከተማ መሆኗን የገላን ኢንዱስትሪ ፓርክ እንደሚያሳይ አስረድተዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኩም ለመካከለኛና ከፍተኛ አምራቾች ምቹ የሥራ ከባቢ በመፍጠር በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በተኪና ወጪ ንግድ የምርት አቅም መገንባት የሚያስችላቸው መሆኑን አብራርተዋል። ከንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ የመጣው አብዱራሂም አስገዶም፤ ኢንዱስትሪ ፓርኩ ኢትዮጵያዊያን መስራትና ለውጥን ማምጣት እንደሚችሉ የሚያሳይ አስደናቂ የልማት ውጤት ነው ብሏል። የኢትዮጵያን ዕድገትና ብልፅግና በልጆቿ ጥረት ዕውን ማድረግ እንደሚቻል የገላን ኢንዱስትሪ ፓርክ ህያው ምስክር መሆኑን ተናግሯል። ሌላኛው ከለሚኩራ የመጣው አስቻለው ሙሉጌታ በበኩሉ፤ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ አምራቾች የሚገጥማቸውን የመስሪያ ቦታ ችግር የሚቀርፍ የልማት አቅም መሆኑን ገልጿል። የጉለሌ ክፍለ ከተማ ነዋሪዋ የጉብኝቱ ተሳታፊ ፍጹም አምሳሉ፤ የኢንዱስትሪ ፓርኩ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ለሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት አቅም የሚሆን የማምረቻ ከባቢ መሆኑን ተናግራለች። የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ በርካታ የመዲናዋ ወጣቶችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ አስደናቂ ፕሮጀክት ነው ያለው ደግሞ ከቂርቆስ ክፍለ ከተማ የመጣው ዮኃንስ ሰለሞን ነው። ፓርኩም የተኪ ምርታማነትን በማሳደግ ለሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ገበያ መቅረብ የሚችሉ የኢንዱስትሪ ምርቶችን የማምረት አቅም እንደሚያጎለብት ማየቱን ተናግሯል።
መንግስት ለህዝብ የገባውን ቃል ይፈፅማል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 21, 2026 87
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ መንግስት ለህዝብ የማይሰራውን ቃል አይገባም፤ ለህዝብ የገባውን ቃል ይፈፅማል ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ዛሬም የኑሮ ውድነትን ለማቃለል፣ ምርት በብዛት ማቅረቢያ እና የግብይት ማዕከላት የማስፋት ስራችን አካል የሆነው 7ኛውን የለሚ ሁለገብ የገበያ ማዕከልን ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል ብለዋል። ማዕከሉ የኑሮ ውድነትን የሚያቃልሉ ዘመናዊ፣ ማሞቂያ እና ማቀዝቀዣ ያላቸው 221 መጋዘኞች፥ የችርቻሮ ሱቆች፥ ሱፐር ማርኬቶች፣ ወፍጮ ቤቶች፣ በአንድ ጊዜ 250 ተሽከርካሪዎችን ማቆም የሚችል ፓርኪንግ፣ ለለሚ ኩራ፣ ለቦሌ እና የካ ክፍለ ከተሞች ነዋሪዎች በአማካይ ቦታ እና ሰሚት ዋና መንገድ ላይ የሚገኝ ምቹ የሆነ ሁለገብ የገበያ ማዕከል ነው ብለዋል። በገበያ ማዕከሉ ማህበረሰቡ ለዕለት ፍጆታ የሚጠቀምባቸውን የሰብል ምርቶች፣ አትክልትና ፍራፍሬዎች፣ የበርበሬ ፣የቅመማቅመም ምርቶች እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን የአንድ ማዕከል የግብይት ስርዓትን እውን ማድረግ መቻሉን ነው ከንቲባዋ የገለጹት። በማዕከሉ የሚቀርቡ ምርቶች ከ15 እስከ 20 በመቶ የዋጋ ቅናሽ የሚሸጥበት፥ ዋጋ የሚያንረውን ህገ-ወጥ የደላላ ሰንሰለት በመበጣጠስ ከአምራቹ ያልተቋረጠ ምርት የሚቀርብበትና የከተማዋ ነዋሪዎችን የኑሮ ጫና እንደሚያቃልል አመልክተዋል። በገበያ ማዕከሉ ከተለያየ ቦታ በኮሪደር ልማት የተነሱ ነዋሪዎችን ጨምሮ ማዕከሉ ያረፈበትን 3 ነጥብ 2 ሄክታር መሬት ለልማት የለቀቁ አርሶ አደሮችም ሱቅ እንዲያገኙ መደረጉንና በዚህም ለነዋሪዎች ሰፊ የስራ እድል መፈጠሩን ተናግረዋል። ለህዝብ የገባነውን ቃል በተግባር እንዲሳካ ጥረት ላደረጉ የዲዛይንና የኮንስትሪክሽን ስራዎች ቢሮ አመራርና ሰራተኞች፣ የንግድ ቢሮ አመራሮችና ሰራተኞች፣ የለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ አመራሮች፣ ቦታው ለልማት እንዲውል ለሰጣችሁ አርሶ አደሮች በራሴና እና በከተማ አስተዳደሩ ስም አመሰግናለሁ ብለዋል።
መንግስት የአፈር ማዳበሪያን በሀገር ውስጥ ለማምረት የጀመረው ጥረት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ የልማት አቅም ነው
May 21, 2026 116
ድሬዳዋ፤ ግንቦት 13/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት የአፈር ማዳበሪያን በሀገር ውስጥ ለማምረት የጀመረው ጥረት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ የልማት አቅም መሆኑን የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) ገልጸዋል። ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የፓናል ውይይት በድሬዳዋ ተካሂዷል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት የዜጎችን ክብርና የሀገርን ሉዓላዊነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ አበረታች ስራዎች እየተሰሩ ነው። ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር በተጀመሩ ኢንሼቲቮች በሚሊየን የሚቆጠሩ ቤተሰቦችን ከልማታዊ ሴፍቲኔት በመላቀቅ ወደ አምራችነት ተሸጋግረዋል ብለዋል። እንዲሁም ከራሳቸው አልፈው ለብሔራዊ የእህል ክምችት አበርክቷቸው መጨመሩን ገልጸው እነዚህን ስራዎች በላቀ ደረጃ በማሳካት የሀገርና የዜጎችን ክብር ለመመለስ የተጀመረው የማዳበሪያ ፋብሪካ ወሳኝ እመርታ መሆኑንም አመልክተዋል። የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ዑመር በበኩላቸው በክልሉ የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የተሰሩ ስራዎች ተጨባጭ ውጤቶች አምጥተዋል። በተለይ ከሃረማያ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ለአርሶ አደሮች የተሰጡ ድጋፎችና ክትትሎች ምርታማነትን በማሳደግ በኩል ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል ነው ያሉት። በሶማሌ ክልል የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን፣ ግብርናና ምግብ ዋስትና ዳይሬክተር ከድር መሐመድ በበኩላቸው ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ተከትሎ የገፀ እና ከርሰ ምድር ሃብቶችን በአግባቡ በመጠቀም አርሶ እና አርብቶ አደሮችን ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር አበረታች ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል። በዚህም ክልሉ ያለው ሰፊ የውሃ እና የእርሻ መሬት እንዲሁም የእንስሳት ሃብት ዜጎችን ከተረጂነት ለማላቀቅ እየዋሉ መሆኑን ገልጸዋል። የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ልማትና ሌሎች የልማት ስራዎች አርብቶና አርሶ አደሩን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የማሸጋገሩን ጉዞ ስኬታማ ማድረጋቸውን የገለፁት ደግሞ በአፋር ክልል አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን የግብርናና ምግብ ዋስትና ከፍተኛ አስተባባሪ ከዲር ኢብራሂም ናቸው። ኢዜአ እና ግብርና ሚኒስቴር በጋራ ያዘጋጁት ሀገር አቀፍ የፓናል ውይይት በቀጣይ የተሻለ እና የተቀናጀ ስራ ለመስራት ያስችላል ብለዋል።
የመዲናዋ የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማዕከል ያደረጉ ናቸው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 21, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማዕከል ያደረጉ መሆናቸውን የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የተገነባውን ሰባተኛውን የለሚ ሁለገብ የገበያ ማዕከል መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ከንቲባዋ በዚሁ ጊዜ፤ በአዲስ አበባ የሚገነቡ ማንኛውም የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት የሚያስገኙ ናቸው ብለዋል። በዚህም ባለፉት አምስት ዓመታት ብቻ የመዲናዋን ነዋሪዎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ያስቻሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። የአዲስ አበባ የልማት ስኬትም ነዋሪዎችና ባለሃብቶች ባደረጉት የዕውቀት፣ የጉልበትና የገንዘብ ድጋፍና ትብብር የመጣ መሆኑንም ተናግረዋል። የለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የገበያ ማዕከልም ምርትና አገልግሎቶችን በብዛትና በጥራት በማቅረብ የገበያ መረጋጋትን የሚፈጥር ወሳኝ መሰረተ ልማት ነው ብለዋል። ይህም የነዋሪዎችን የኑሮ ጫና በማቃለል ምርትን በብዛትና በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ እንደሚያስችል ጠቅሰዋል። ማዕከሉ ምርቶችን በቀጥታ ከእርሻ እንዲገቡ በማድረግ አላስፈላጊ የምርት ብክነትን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ ያስችላል ብለዋል። ማዕከሉ የጥራጥሬ፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ የቅባት እህሎችና ሌሎች መሠረታዊ የፍጆታ ዕቃዎችን በጥራት ማቅረብ የሚያስችል ዘመናዊ መሰረተ ልማት የተሟላለት መሆኑንም ተናግረዋል።
ከተረጂነት ለመውጣት በተተገበሩ ኢንሼቲቮች የራስን ችግር በራስ መፍታት እንደሚቻል ማሳየት ተችሏል
May 21, 2026 108
ድሬደዋ፤ ግንቦት 13/2018(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ከተረጂነት ለመውጣት በተተገበሩ የተሳኩ ኢንሼቲቮች የራስን ችግር በራስ አቅም መፍታት እንደሚቻል በተግባር ማሳየት መቻሉን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀውና "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" የሚል መሪ ሃሳብ ያለው የውይይት መድረክ በድሬዳዋ ከተማ ተካሂዷል። ዶ/ር ቢቂላ ሁሪሳ በመድረኩ እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ እየተተገበረ የሚገኘው ከተረጂነት ለመውጣት ያለመው መርሃ ግብር ተጨባጭና ተስፋ ሰጪ ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል። ከሁሉም በላይ አጀንዳው በተግባር መሬት መውረዱና በአመራሩ እና በህዝቡ ዘንድ ጠንክሮ ከተሰራ ከተረጂነት መውጣት እንደሚቻል ትልቅ መነቃቃትን ፈጥሯል ብለዋል። በየደረጃው የሚገኘው አመራር በአካባቢው ያለውን የተፈጥሮ ጸጋና አቅም በመለየት፣ ህዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት እንቅስቃሴዎችን መጀመሩን ጠቅሰዋል። ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገው እያንዳንዱ ጥረት ከመንግስት የልማት ፕሮጀክቶች እና ዋና ዋና ኢንሼቲቮች ጋር ተናቦ መተግበሩ ለአጀንዳው ስኬታማነት ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ገልፀዋል። በየአካባቢው ከተረጂነት መውጫ የትኩረት አቅጣጫዎችን ለይቶ ስልጠና መስጠት መቻሉና የልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራምን ከአካባቢ ልማት ጋር ማስተሳሰር መቻሉ ውጤታማ አድርጎታል ነው ያሉት። ባለፉት ዓመታት በተሰሩ የተቀናጁ ስራዎች የሚከሰቱ ችግሮች በህዝብ ላይ ሊያደርሱ የሚችሉትን ስጋቶች መቀነስ ተችሏል ያሉት ሚኒስትሩ፤ ይህም በበርካታ ተጋላጭ ወረዳዎች ላይ በተግባር መረጋገጡን አንስተዋል። በዚህም መሠረት በርካታ ዜጎች ከተረጂነት ወጥተው፣ ትርፍ አምራች በመሆን ሀብት ማፍራት የጀመሩ ሲሆን፤ ከራሳቸው ፍጆታ አልፈው ለሌሎች መትረፍ የቻሉበት ደረጃ ላይ መደረሱን አብራርተዋል። ከእንስሳት ሀብት ልማት አንጻርም በተሻለ ሁኔታ ውጤታማ የሆኑ በርካታ የአርብቶ አደር አካባቢዎች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ ለሌሎች አካባቢዎች የእንስሳት መኖ ማቅረብ የጀመሩ መኖራቸውን በአብነት አንስተዋል። በአጠቃላይ በመርሃ ግብሩ የተከናወኑ ስራዎች ኢትዮጵያ የራስን ችግር በራስ የመፍታት አቅም እንዳላት በተግባር ያረጋገጠችበት ታሪካዊ ጉዞ መሆኑን ሚኒስትሩ አስረድተዋል። በመርሃ ግብሩ አማካኝነት በገጠር አካባቢዎች የመሰረተ ልማት ተደራሽነትን በሰፊው ማስፋፋት መቻሉ፣ በተለይም የሴቶች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እንዲያድግ ተደርጓል ብለዋል። በዚህም ህብረተሰቡ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን የመቋቋም አቅሙ ጎልብቷል ነው ያሉት። በተሰሩ ስራዎች አደጋዎችን መቋቋም ተጀምሯል፤ ኢትዮጵያም የራሷን ችግር በራሷ መፍታት እንደምትችል ለዓለም ማሳየት ጀምራለች ሲሉ ተናግረዋል።
በክልሉ የመንግስት ሰራተኛው ፈጣንና ፍትሃዊ አገልግሎት በመስጠት የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ ይሰራል
May 21, 2026 79
ባህርዳር፤ ግንቦት 13/2018(ኢዜአ)፦ የመንግስት ሰራተኛው ፈጣንና ፍትሃዊ አገልግሎት በመስጠት የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ የድርሻውን መወጣቱን እንደሚቀጥል የአማራ ክልል ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ባንችአምላክ ገብረማርያም ገለጹ። የመንግስት ሰራተኛውን በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የሚያወያይ መድረክ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። የቢሮ ኃላፊዋ በወቅቱ እንደገለፁት፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉና ለሀገር እድገት ዘላቂ መሰረት የጣሉ የልማት ፕሮጀክቶች መተግበራቸውን ገልፀዋል። በየደረጃው እየተመዘገበ ላለው ውጤት የመንግስት ሰራተኛው ፈጣንና ፍትሐዊ አገልግሎት በመስጠት የልማት ስራዎች በመደገፍ የድርሻውን መወጣቱን መቀጠል ይገባዋል ነው ያሉት። ኮሪደርን መሰረት ያደረገው የከተሞች ልማት፣ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት፣ የአረንጓዴ አሻራ፣ የበጋ ስንዴና ሌሎች ኢንሼቲቮች በክልሉ ውጤት ከተመዘገበባቸው መስኮች መካከል ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። በትምህርትና በጤናው ዘርፎችም ይታዩ የነበሩ ችግሮችን ለማቃለል በተከናወኑ ተግባራት ጤናማ፣ ብቁና ሀገር ወዳድ ዜጋ ማፍራት እየተቻለ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል። የተጀመሩ የልማት ተግባራትን አጠናክሮ ለማስቀጠል የመንግስት ሰራተኛው የድርሻውን መወጣት ይጠበቅበታል ሲሉ አስገንዝበዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል አቶ ስንታየሁ ስንሻው እና አቶ ላመስግን አዳነ እንደገለጹት፤ የክልሉን የሀገር ልማትና ዕድገት በማፋጠን የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ኃላፊነታቸውን በመወጣት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይም ፈጣን፣ ቀልጣፋና ፍትሐዊ አገልግሎት መስጠት ላይ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ነው የገለጹት።
በከተማዋ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ማደግ ሰፊ የሥራ ዕድል ፈጥሮልናል -የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪዎች
May 21, 2026 128
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦የወላይታ ሶዶ ከተማ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ማደግ ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ በከተማዋ በተለያየ ዘርፍ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነዋሪዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በወላይታ ሶዶ ከተማ ያለው የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ እያደገ በመምጣቱ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ አድርጓቸዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወጣት ገዛኸኝ ገብሬ እና አቶ አበራ አርካ፤ በኢንዱስትሪ ዘርፍ በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል የተሻለ ገቢ እያገኙና ኑሯቸውም እየተሻሻለ መምጣቱን ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በአነስተኛ ገቢ ይተዳደሩ እንደነበር አስታውሰው፣ በከተማው እየተነቃቃ የመጣው የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ለነዋሪዎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ተጨማሪ አቅም መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል ከሚያገኙት ገቢ በመቆጠብ የራሳቸውን ሥራ የመፍጠር ዕቅድ እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ በሪል ስቴት የግንባታ ዘርፍ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ዙፋን ሰይድ፣ ሚናሴ ዲዲምስ እና ኤልሳዬ ምልኪያስ በበኩላቸው እንዳሉት፤ ቀደም ሲል የነበረው የሥራ ዕድል ጠባብ በመሆኑ ጊዜያቸውን በአልባሌ ቦታ ያሳልፉ ነበር። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በከተማዋ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን ተከትሎ የተጀመሩ የግንባታ ፕሮጀክቶች የአካባቢያቸውን ገጽታ የሚቀይሩ ከመሆን ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ተናግረዋል። እነሱም ባገኙት የሥራ ዕድል ተጠቅመው ቤተሰቦቻቸውን ጭምር እያገዙ መሆናቸውን ገልጸው፣ ለአካባቢው ልማት ቀጣይነት የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁነታቸውን አረጋግጠዋል። ከተማ አስተዳደሩ ባደረገላቸው ድጋፍ በ40 ሚሊዮን ብር ካፒታል ወደሥራ እንደገቡ የተናገሩት ደግሞ የራማ ፋሚሊ ፒቪሲ፣ ኤች ዲፒ እና ፕላስቲክ ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሳዲቅ አብዱልሃዲ ናቸው፡፡ በአሁን ወቅት ካፒታላቸው ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ መድረሱን ጠቅሰው ከ40 ለሚበልጡ ዜጎችም ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል፡፡ የኢያሱ ያዕቆብ ኮንስትራክሽን ሥራ አስኪያጅና ባለቤት ኢንጂነር ኢያሱ ያዕቆብ በበኩላቸው፣ የከተማ አስተዳደሩ ለሪል ስቴት ግንባታ ያቀረቡትን ጥያቄ በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጽደቁ በ500 ሚሊዮን ብር ካፒታል የመጀመሪያ ዙር የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል። በዚህም ከ370 በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው ወጣቶች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል። ድርጅታቸው በከተማው የሚስተዋለውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በቅንጀት እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ 29 የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ወደሥራ መግባታቸውን የገለጹት ደግሞ የወላይታ ሶዶ ከተማ ኢንቨስትመንት ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቸርነት ተስፋዬ ናቸው። ኢንቨስትመንቶቹ በአገልግሎት፣ በኢንዱስትሪ፣ በግንባታና ሌሎች ዘርፎች ላይ ያተኮሩ እንደሆነም አመልክተዋል። በዚህም ከ1 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል ያሉት ኃላፊው፣ ወጣቶችም የቴክኖሎጂ እና የክህሎች አቅማቸውን ለማሳደግ ተጨማሪ ዕድል አግኝተዋል ብለዋል።
በምግብ ራሱን የቻለ ትውልድ የመገንባት ጥረት የሀገርን ክብርና ሉአላዊነት እውን የማድረግ ቁልፍ አጀንዳ ነው
May 21, 2026 142
ድሬዳዋ ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ ከተረጅነት በመውጣት በምግብ ራሱን የቻለ ትውልድ የመገንባት ጥረት የሀገርን ክብርና ሉአላዊነት እውን የማድረግ ቁልፍ አጀንዳ መሆኑን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ የተዘጋጀው የውይይት መድረክ በድሬዳዋ ተካሄዷል። በመድረኩ ላይ የውይይት መነሻ ሐሳብ ያቀረቡት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)፤ ከተረጅነት የመውጣትን ጉዳይ መንግስት ወሳኝ ሀገራዊ አጀንዳ አድርጎ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በምግብ ራሱን የቻለ ትውልድ የመገንባት ጥረት የሀገርን ክብርና ሉአላዊነት እውን የማድረግ ቁልፍ አጀንዳ መሆኑን አንስተው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በትውልድ ቅብብሎሽ የመጣውን በእርዳታ የመኖር የጥገኝነት አመለካከት አከርካሪ በመስበር የሀገርን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የተጀመረውን አበረታች ጉዞ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር፣ ሂደቱን በሁለንተናዊና በተሟላ አስተሳሰብ መምራት ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ በቂና የተሟላ የውሃ ሀብት፣ የተማረና አምራች የሆነ ወጣት የሰው ኃይል እንዲሁም ለም የመሬት ፀጋዎች ያሉባት ሀገር በመሆኗ በማልማት እድገትና ማንሰራራትን ማስቀጠል ይቻላል ሲሉ ተናግረዋል። ከተረጂነት ለመላቀቅ የሚያግዙ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እሴቶችን በመጠቀም፣ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በፍጥነትና በፈጠራ የተመሩ የግብርና ልማት ስራዎች በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ ተጨባጭና እመርታዊ ለውጥ እያመጡ ነው ብለዋል። በምግብ ራስን የመቻል ራዕይ ከቤተሰብ ኑሮ ለውጥ እንደሚጀምር ጠቅሰው፤ ዜጎች በሰፊው አምራች እንዲሆኑ፣ የተመረተውን በአግባቡ በመጠቀምና በመቆጠብ መጠቀም እንዲችሉ እንዲሁም ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገር እንዲችሉ መደገፍ አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። ዋናው መሠረታዊ ጉዳይም ያሉንን አቅሞች በመለየትና ህዝብን ወደ ላቀ ምርታማነት ደረጃ በማሸጋገር በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ አስተሳሰብና አተገባበር በላቀ ደረጃ ማስቀጠል መቻል መሆኑን አስታውቀዋል።
በክልሉ ፕሮጀክቶችን ባጠረ ጊዜ በማጠናቀቅ የሕዝቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ነው
May 21, 2026 148
ዓለምገበያ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የልማት ፕሮጀክቶችን ባጠረ ጊዜ በማጠናቀቅ የሕዝቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። የውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በስልጤ ዞን ሳንኩራ ወረዳ ያስገነባው የብዝኃ መንደር የንጹሕ መጠጥ ውኃና ሳኒቴሽን ፕሮጀክት ተመርቋል። ፕሮጀክቱ ከ430 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበት ሲሆን፣ በ11 ቀበሌዎች ከ31 ሺሕ በላይ ሰዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑ ተገልጿል። ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ መንግሥት የልማት ፕሮጀክቶችን ግንባታ ጀምሮ ባጠረ ጊዜ በማጠናቀቅ የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል። ለዚህም አዲስ የተመረቀው የሳንኩራ የብዝኃ መንደር የንጹሕ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን ጠቁመዋል። ፕሮጀክቱ ለረዥም ጊዜ አገልግሎት እንዲሰጥም የአካባቢው ማኅበረሰብ በተገቢው መንገድ የመንከባከብ ኃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል። የውኃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ለሰው ልጆች ሕልውና መሠረት በሆነው የንጹሕ መጠጥ ውኃ አቅርቦት ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የውኃ ሀብትን በብቃት በማስተዳደርና ከብክለት በመጠበቅ ለማኅበረሰቡ ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል አሠራር ተዘርግቶ እየተተገበረ እንደሚገኝም አክለዋል። የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘይኔ ቢልካ፣ ባለፉት 5 ዓመታት በመንግሥትና በማኅበረሰቡ ተሳትፎ የዞኑን የንጹሕ መጠጥ ውኃ ሽፋን ለማሳደግ ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል። በመንግሥት ድጋፍ 25 የንጹሕ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክቶች ተገንብተው ከ246 ሺሕ በላይ ሰዎች ተጠቃሚ ሆነዋል ብለዋል። በዚህ በጀት ዓመት ብቻ ከማኅበረሰቡ ከ298 ሚሊዮን ብር በላይ በማሰባሰብ የውኃ አቅርቦት ችግርን የሚቀርፉ በርካታ ሥራዎች ተከናውነዋል ነው ያሉት። በሳንኩራ ወረዳ የጀጀብቾ ለምለም ቀበሌ ነዋሪዋ ወይዘሮ ፈቱ ኮርማ፤ ከዚህ ቀደም በነበረው የንጹሕ መጠጥ ውኃ እጥረት ምክንያት ረዥም ርቀት ለመጓዝ ይገደዱና ለተለያዩ እንግልቶች ይዳረጉ እንደነበር አስታውሰዋል። ዛሬ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት የጀመረው ፕሮጀክት ይህንን ችግራቸውን በዘላቂነት የሚፈታላቸው በመሆኑ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል። በዚሁ የምረቃ መርሐ ግብር ላይ የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና የወረዳው ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በዞኑ የሻይ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
May 21, 2026 94
መቱ፤ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦በኢሉአባቦራ ዞን የሻይ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የዞኑ አስተዳደር ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። በዞኑ 974 ሄክታር አዲስ መሬት ላይ የሻይ ችግኝ የሚተከል መሆኑም ነው የተገለጸው፡፡ የዘንድሮው የሻይ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የዞንና የክልል ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት በኢሉአባቦራ ዞን መቱ ወረዳ፣ ቀዎና ጫቱ ቀበሌ በይፋ ተጀምሯል። በችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ላይ የኢሉአባቦራ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ እንደገለጹት፤ በዞኑ የሻይ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። ዞኑ ለልማቱ ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም የሻይ ችግኞችን በስፋት በማዘጋጀትና ለአርሶ አደሩ በማሰራጨት የመትከል ስራ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ዘንድሮ በአምስት ወረዳዎች በሚካሄደው የሻይ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር 974 ሄክታር አዲስ መሬት ለማልማት ታቅዷል ብለዋል። በዞኑ እንደ አንድ ትልቅ የግብርና ኢኒሼቲቭ ተደርጎ የተጀመረውን የሻይ ልማት በኩታ ገጠም አሰራር በማስፋፋት ምርታማነትን ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ዋና አስተዳዳሪው አውስተዋል። ባለፉት ዓመታት የተተከሉት ችግኞች አሁን ላይ ለለቀማ የደረሱ በመሆናቸው፣ አርሶ አደሩ ምርቱን በወቅቱ መሸጥ እንዲችል ከጉማሮ ሻይ ፋብሪካ ጋር የገበያ ትስስር መፈጠሩን አቶ እንዳልካቸው ገልጸዋል። ከዚህም በተጨማሪ ልማቱ በተስፋፋባቸው ወረዳዎች አዲስ የሻይ ፋብሪካ የሚቋቋምበትን ሁኔታ ለማመቻቸት አስተዳደሩ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ነመራ ቡሊ በበኩላቸው፤ የክልሉ መንግሥት የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በአጭር ጊዜ ያረጋግጣሉ ብሎ ካተኮረባቸው የግብርና ኢኒሼቲቮች መካከል የሻይ ልማት ግንባር ቀደም ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸዋል። የሻይ ምርት ለውጭ ገበያ ጭምር የሚቀርብ በመሆኑ ለአገሪቱ የውጭ ምንዛሪ ግኝት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ገልጸው፤ በተለይም በኢሉአባቦራ፣ በቡኖ በደሌና በጂማ ዞኖች ባለፉት ዓመታት የተጀመረውን የሻይ ልማት ስራ ይበልጥ ለማስፋት የክልሉ መንግሥት አቅጣጫ አስቀምጦ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በመቱ ወረዳ የልማቱ ተሳታፊ አርሶ አደሮች መካከል አቶ ዋሴ ለማና አቶ ግርማ ታምሩ በሰጡት አስተያየት፤ የሻይ ልማት የተሻለና አስተማማኝ ገቢ የሚያስገኝ በመሆኑ በልማቱ ላይ ያላቸው ተነሳሽነት በእጅጉ ማደጉን ተናግረዋል። ቀደም ሲል የተከሏቸውን የሻይ ተክሎች በሚገባ በመንከባከብ፣ ምርቱን በዘላቂነት በመሰብሰብና ለፋብሪካ በማቅረብ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለማድረግ በትጋት እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።
የምርት ጥራት ደረጃ ማረጋገጫ መተግበሪያው የኢትዮጵያን የንግድ አፈፃጸም ውጤታማነት የሚያልቅ ነው
May 21, 2026 108
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦አዲሱ የምርት ጥራት ደረጃ ማረጋገጫ መተግበሪያ የኢትዮጵያን የንግድ አፈፃጸም ውጤታማነት የሚያልቅ መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) እና የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስትቲዩት ዋና ዳይሬክተር መሠረት በቀለ (ዶ/ር) በተገኙበት የምርት ጥራት ደረጃን በኦንላይን ማረጋገጥ የሚያስችል መተግበሪያ ተመርቋል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ የምርትና አገልግሎት ጥራትን ማረጋገጥ የመደመር መንግስት ማዕከል ነው ብለዋል። በዚህም ባለፉት የለውጥ ዓመታት የኢትዮጵያን የንግድ ሥርዓት በማዘመን የምርት ጥራትን ከውጤታማ አፈፃጸም የሚያጣጥም ስኬት መገኘቱን ገልጸዋል። አዲሱ የምርት ጥራት ማረጋገጫ የኦንላይን መተግበሪያም አገልግሎትና የምርት ጥራቶችን በላቀ አፈፃጸም መምራት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። እስከ አሁንም በንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር በርካታ አገልግሎቶች በዲጂታል ሥርዓት እየተሰጡ መሆናቸውን አንስተዋል። ይህም የኢትዮጵያን የንግድ ሥርዓት በማዘመን አይነተኛ ሚና እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት ለውጤት የበቃው የምርት ጥራት ደረጃ ማረጋገጫ መተግበሪያም የወጪና የገቢ ንግድን በከፍተኛ ደረጃ የሚያሳልጥ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት የምርቶችን የጥራት ደረጃ በኦንላይን ማረጋገጥ የሚያስችል መተግበሪያ ይፋ አደረገ
May 21, 2026 72
አዲስ አበባ፤ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት የምርቶችን የጥራት ደረጃ በኦንላይን ማረጋገጥ የሚያስችል መተግበሪያ ይፋ አድርጓል። መተግበሪያው የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) እና የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር መሠረት በቀለ (ዶ/ር) በተገኙበት ተመርቆ ወደ ስራ ገብቷል። የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር መሠረት በቀለ (ዶ/ር)፥ መተግበሪያው ምርቶችን በኦንላይን ስርዓት በመለየትና በመተንተን የጥራት ደረጃቸውን ማረጋገጥ እንደሚያስችል ገልጸዋል። ይህ መተግበሪያ ህብረተሰቡ ያለምንም መጭበርበር ምርቶችን እንዲሸምት እንደሚያስችል ጠቁመዋል። ይህ የዲጂታላይዜሽን ስርዓት የኢትዮጵያን የምርትና አገልግሎት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት እንደሚጨምር ተናግረዋል። ወቅቱን የዋጀ የደረጃ ትግበራ ስራዎችን በጥራትና ፍጥነት ተደራሽ ለማድረግ አይነተኛ ሚና እንደሚኖረውም እንዲሁ። መተግበሪያውን ማንኛውም ሰው ከአፕ ስቶር ወይም ፕላይ ስቶር አውርዶ በመመዝገብ መጠቀም እንደሚችል ገልጸዋል። የኦንላይን መተግበሪያው አስተማማኝነት በሚመለከተው አካል መረጋገጡን ጠቁመዋል። ኢንስቲትዩቱ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ያከናወናቸውን አጠቃላይ ተቋማዊ የሪፎርም ስራዎችንም አስመርቋል።
በእርሻ ኢንቨስትመንት መስክ የተሰማሩ ዜጎች በተፈጠረላቸው የስራ እድል ተጠቃሚ ሆነዋል
May 21, 2026 63
አብርሃጅራ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በተፈጠረላቸው የስራ እድል ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ እንደሚገኙ በምዕራብ ጎንደር ዞን በእርሻ ኢንቨስትመንት መስክ የተሰማሩ ዜጎች ተናገሩ ። በዞኑ ምዕራብ አርማጭሆ በድርማጋ የእርሻ ኢንቨስትመንት ስራ አስኪያጅ የሆነው ወጣት አስቻለው ደሴ ለኢዜአ እንደገለጸው ፤ ባለፉት ሶስት ዓመታት በድርጅቱ በተፈጠረለት ቋሚ የስራ እድል ተጠቃሚ ሆኗል። "በሚከፈለኝ ወርሃዊ ደመወዝና ዓመታዊ ክፍያ ቤተሰቤን ከማስተዳደር ባለፈ በዘርፉ የራሴን ስራ ለመጀመር ዝግጅት እያደረኩ ነው" ሲል ገልጿል። በዞኑ የተለያዩ ወረዳዎች በመዘዋወር በእርሻ ልማት የስራ ዕድል ተጠቃሚ የሆነው ወጣት ካሳሁን ደሳለኝ በበኩሉ፣ በዘር፣ በአረምና በሰብል ስብሰባ ወቅት በአካባቢው በሚፈጠረው የስራ እድል እንደሚሰማራ ነው የሚናገረው። በተለይም በሰሊጥ፣ በጥጥ፣ አኩሪ አተርና ሌሎች ሰብሎች በሚሰብሰቡበት ወቅት እስከ 180 ሺህ ብር እንደሚያገኝ ነው የተናገረው። ባገኘው ገቢም አነስተኛ የሸቀጣ ሸቀጥ ሱቅ በመክፈት የቤተሰቦቹን ኑሮ ከማሻሻል ባለፈ ተጨማሪ ሀብት በመፍጠር ሒደት ላይ መሆኑን አስረድቷል። ከመንግስት በተሰጣቸው 481 ሄክታር መሬት ላይ ሰሊጥ፣ ጥጥ፣ አኩሪ አተርና ሌሎች ምርቶችን እያመረቱ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በዘርፉ የተሰማሩት አቶ ቴዎድሮስ አለማየሁ ናቸው። በእርሻ ስራው በየዓመቱ ለሁለት ሺህ ዜጎች ጊዜያዊ ፤ለ29 ዜጎች ደግሞ ቋሚ የስራ እድል በመፍጠር ከራሳቸው አልፎ ወጣቶችን ተጠቃሚ እያደረጉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የምዕራብ ጎንደር ዞን ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኃላፊ ተወካይ አቶ ዳንዔል አለሙ በበኩላቸው፣ በዞኑ ያለው ሰፊ የእርሻ መሬትና ተስማሚ የአየር ንብረት ለእርሻ ኢንቨስትመንት ተመራጭ እንዲሆን አድርጎታል ። በርካታ ባለሃብቶች ወደ አካባቢው በመምጣት በዘርፉ በመሳተፍ ለወጭ ንግድ የሚሆኑ ምርቶች ላይ እየሰሩ እንደሚገኙም ነው የገለጹት ። በዞኑ በእርሻ ኢንቨስትመንት የተሰማሩ 976 ባለሃብቶች በዘር፣ በአረምና ሰብል ስበሰባ ወቅት 370 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ጊዜያዊና ቋሚ የስራ እድል እየፈጠሩ መሆኑን ገልፀዋል።
በዞኑ በመጪው መኸር ከ 641 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ የሰብል ዘር ለመሸፈን የሚያስችል ዝግጅት ተደርጓል
May 21, 2026 68
ባህር ዳር፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ጎንደር ዞን በመጪው መኸር ከ641 ሺህ ሄክታር በላይ መሬትን በተለያየ የሰብል ዘር ለመሸፈን የሚያስችል ዝግጅት መደረጉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ አስፋው ይልማ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል በትኩረት እየተሰራ ነው። በዚህም ከ641 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ ደጋግሞ የማረስና ሌሎች የቅድመ ዝግጅት ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በዘር ከሚሸፈነው መሬትም ከ28 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ጠቁመው አሁን ላይ እንደ በቆሎ ያሉ ሰብሎችን መዝራት መጀመሩን ተናግረዋል። የማዳበሪያና የምርጥ ዘር ግብዓትን በመጠቀም፣ የሜካናይዜሽንና አዳዲስ አሰራሮችን በመተግበር ላይ በማተኮር የታቀደውን ምርታማነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራ ገልጸዋል። በዘር ከሚሸፈነው መሬት ውስጥ 65 በመቶ የሚሆነው መሬት በኩታ ገጠም አሰራር በቢራ ገብስ፣ በሩዝ፣ በስንዴ፣ በጤፍና በበቆሎ ዘሮች እንደሚሸፈን አስረድተዋል። ይህም በሄክታር ከ41 ነጥብ 4 ኩንታል ያልበለጠ የነበረውን ምርታማነት ወደ 44 ነጥብ 3 ኩንታል ለማሳደግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። በሰብል ልማቱም 465 ሺህ አርሶ አደሮች እንደሚሳተፉ ጠቁመው፤ በየደረጃው ያለው የዘርፉ አመራርና ባለሙያም አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። በዞኑ ፋርጣ ወረዳ ሳርና ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር የማታ ቢሰጥ፤ ከአንድ ሄክታር በላይ ማሳቸውን በዘር በመሸፈን ከ42 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በዚሁ ወረዳ የማይናት ቀበሌ አርሶ አደር ንጋቴ ጎሸ በበኩላቸው፤ አንድ ሄክታር ማሳቸውን በቢራ ገብስ በማልማት 45 ኩንታል ለማምረት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። ምርታማነቱን ለማሳደግም ሁለት ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ቀደም ብለው ገዝተው ማስቀመጣቸውን ጠቁመው በቀጣይም ምርጥ ዘርና ተጨማሪ ማዳበሪያ ገዝተው እንደሚጠቀሙም ገልጸዋል። በዞኑ ባለፈው የመኸር ወቅት ከ26 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ማምረት መቻሉን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የማዳበሪያ ፋብሪካ በሀገራችን መገንባቱ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ያፋጥናል
May 21, 2026 114
ድሬደዋ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ የማዳበሪያ ፋብሪካ በሀገራችን መገንባቱ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በማፋጠን ከፍተኛ ሚና አለው ሲሉ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) ተናገሩ። “ከተረጂነት ወደ ምርታማነት” በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የተዘጋጀ የፓናል ውይይት በድሬዳዋ ከተማ እየተካሄደ ነው። ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፥ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የኅልውና ጉዳይ ነው። የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥም ግብዓቶቹ በሀገራችን ይገኛሉ ነው ያሉት። ማዳበሪያ በሀገር ውስጥ እንዲመረት መንግሥት በልዩ ትኩረት እየሠራ መሆኑን አስገንዝበዋል። የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጉዞ በማፋጠን ከፍተኛ ሚና እንዳለውም ነው ያስረዱት። አርሶ አደሮች በክላስተር እና በምርምር የተደገፉ ሰብሎችን በማምረት ትርፍ አምራች ሆነው ስኬታማ እንዲሆኑ እየተሠራ መሆኑንም አስታውቀዋል። አንድም መሬት ጾም ማደር የለበትም በሚል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል ብለዋል። ክልሎችም በመተጋገዝ፣ተሞክሯቸውን በመለዋወጥ ከተረጅነት ወደ አምራችነት ለመሸጋገር የሚደረግ ጥረትን ማዳበር እንዳለባቸው አመላክተዋል። እንደ ሀገር ከተረጅነት ወደ አምራችነት መሸጋገር የማይቻልበት ምንም ምክንያት የለም ሲሉም በአጽንዖት ገልጸዋል።
በኦሮሚያ ክልል በበልግ እርሻ የታቀደውን ምርት ለማግኘት የሰብል እንክብካቤና ጥበቃ ላይ ትኩረት ተደርጓል
May 21, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በበልግ እርሻ የተዘሩ ሰብሎችን እንክብካቤና ጥበቃ በማድረግ የታቀደውን ምርት ለማግኘት ትኩረት መደረጉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ባሪሶ ፈይሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በበልግ አዝመራ ከለማው 1 ነጥብ 9 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ከ46 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዷል። ዘንድሮ የተከናወነው የበልግ እርሻ ስራ ከዕቅድ በላይ መፈጸሙን የገለጹት ኃላፊው፣ ለዚህ ስኬት ዋነኛው ምክንያት ያለውን አቅም አሟጦ መጠቀም በመቻሉ እንደሆነ አብራርተዋል። ለአርሶ አደሮቹ ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ግብዓትና የግብርና ቴክኖሎጂዎች መቅረባቸውን አስታውሰው በተለይ የዘንድሮው የበልግ አዝመራ የዝናብ ስርጭቱ የተሻለ በመሆኑ ሰብሉ በጥሩ ቁመና ላይ እንዳለ አመላክተዋል። በክልሉ በአሁኑ ወቅት በበልግ አዝመራው የታቀደውን ምርት ለማግኘት የሰብል ጥበቃና የእንክብካቤ ስራ ላይ ልዩ ትኩረት በመስጠት ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። ለዚህም ይረዳ ዘንድ የፀረ-አረምና የተባይ ኬሚካሎች ለአርሶ አደሮቹ በስፋት እየቀረቡ መሆኑን አስታውቀዋል። እንዲሁም አርሶ አደሮቹ ሰብሉን በቤተሰብ ደረጃና ከአካባቢያቸው ነዋሪዎች ጋር ሆነው በጋራ እየተንከባከቡ መሆኑን ገልጸዋል። በበልጉ የለማው ሰብል ላይ ጉዳት ሊያደርሱ የሚችሉ እንደ ግሪሳ ወፍ እና መሰል ተባዮችን አስቀድሞ ለመከላከል፣ በዘርፉ ባለሙያዎች አማካኝነት አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን ኃላፊው አክለው ገልጸዋል። ለዘንድሮው የበልግ እርሻ ስኬታማነት በየደረጃው የሚገኙ የግብርና ባለሙያዎችና አመራሮች የበኩላቸውን እየተወጡ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ የእርሻ መሬትን አስቀድሞ ከማዘጋጀት ጀምሮ ለአርሶ አደሩ ቀጣይነት ያለው ሙያዊ ድጋፍና ክትትል መደረጉንም ነው የጠቀሱት። በክልሉ የበልግ እርሻ በስፋት ከሚከናወንባቸው 11 ዞኖች መካከል ምስራቅ ቦረና፣ ጉጂ፣ አርሲ፣ ምስራቅ እና ምዕራብ ሐረርጌ፣ ምስራቅ ባሌ እና ምስራቅ ሸዋ ዞኖች ይጠቀሳሉ።
ሀገር የተሟላ ክብርና ሉአላዊነት ሊኖራት የሚችለው ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት መውጣት ሲቻል ነው
May 21, 2026 100
ድሬዳዋ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገር የተሟላ ክብርና ሉአላዊነት ሊኖራት የሚችለው ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት መውጣት ሲቻል ነው ሲሉ በድሬዳዋ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማእረግ የመንግስት ተጠሪ ኢብራሂም የሱፍ ገለጹ። "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና ግብርና ሚኒስቴር የተዘጋጀው የውይይት መድረክ በድሬዳዋ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት በድሬዳዋ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማእረግ የመንግስት ተጠሪ ኢብራሂም የሱፍ፤ በለውጡ ዓመታት በመደመር እሳቤ የህዝብን ተጠቃሚነት እውን ያደረጉና ሀገርን ወደ ማንሰራራት የወሰዱ ስኬቶች ተመዘግበዋል ብለዋል። በተለይም በስንዴ ልማት የላቀ ስኬት ስለመመዝግቡ አንስተው በተለያዩ የግብርና ኢንሸቲቮች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የመሸጋገር ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን አንስተዋል። ለውጡ እየተመራበት ያለው የመደመር እሳቤ የዜጎችን ተጠቃሚነት እንዲሁም የሀገርን እድገትና ማንሰራራት ለማሳለጥ ያስቻለ ስኬታማ አቅጣጫ መሆኑን ያሳየ መሆኑንም ተናግረዋል። በምግብ ራስን የመቻል ጥረት የሀገር ክብርና የትውልድ ዋስትና መሰረት መሆኑን በፅኑ በማመን መንግስት ለስኬቱ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ከተረጅነት የመውጣት ጉዳይ የዜጎችን ክብርና የሀገርን የወደፊት እጣ ፋንታ የሚወስን ወሳኝ ሀገራዊ አጀንዳ በመሆኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ ስለመሆኑ ተናግረዋል። በመሆኑም ሀገር የተሟላ ክብርና ሉአላዊነት ሊኖራት የሚችለው ከተረጅነት መውጣት ሲቻል መሆኑን አንስተው የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰይፈ ደርቤ፤ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመተባበር የሚካሄዱ መሰል መድረኮች ለሀገር የሚጠቅሙ ጥልቅ ሃሳቦች የሚነሱበት መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም እንደ ሀገር ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረጉ ጥረቶችንና የዜጎችን ብሩህ ተስፋ የሚያሳዩ የይዘት ስራዎችን በሚዲያ በስፋት ተደራሽ ማድረግ እንደሚገባ አንስተዋል። ኢትዮጵያ ከተረጂነት በመውጣት ምርታማነትን በማሳደግ እድገትና ማንሰራራቷ ቀጣይነት እንዲኖረው በስፋትና በጥልቀት የይዘት ስራዎችን ተደራሽ ማድረግ ይገባል ብለዋል። በመድረኩ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)፣ የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መሥተዳድር ሮዛ ዑመር፣ የፌዴራልና የክልል የመንግስት የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም ከድሬዳዋ አሥተዳደር፣ ከሶማሌ፣ ሐረሪ እና አፋር ክልሎች የተውጣጡ በርካታ አርሶ አደሮች ተገኝተዋል።
ከተረጂነት መላቀቅን የክብር ጉዳይ አድርጎ መትጋት ይገባል - ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)
May 21, 2026 135
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ ከተረጂነት መላቀቅ የሀገራዊ ሉዓላዊነትና የክብር ጉዳይ በመሆኑ ለዚሁ ስኬት በቅንጅት መትጋት እንደሚገባ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። “ከተረጂነት ወደ ምርታማነት” በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢፌዴሪ ግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የተዘጋጀ የፓናል ውይይት በድሬዳዋ ከተማ እየተካሄደ ነው። ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) በዚሁ መድረክ ላይ ባቀረቡት የፓናል ውይይት መነሻ ጽሑፍ፤ በዕርዳታ እህል ትውልድን ማስቀጠል እንደማይቻል ገልፀዋል። የተሟላ ሉዓላዊነት ማለት፤ የብሔራዊ ደኅንነት ሉዓላዊነት፣ የምግብ ሉዓላዊነት፣ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት፣ የፖሊሲ ሉዓላዊነት፣ የባህልና የማንነት ሉዓላዊነት መሆኑንም አብራርተዋል። በዚህ መነሻም እንደሀገር ተረጂ ሆኖ፤ ልማትን፣ ፍላጎትን፣ ነጻነትን እንዲሁም ትውልድን ማስቀጠል የማይታሰብ ነው ብለዋል። ዕርዳታ ሰጪዎች ፍላጎታቸውንም እንድንፈፅም ማስገደዳቸው እንደማይቀር ታውቆ፤ ከተረጂነት በመውጣት አምራች መሆን የተሟላ ሉዓላዊነት ጉዳይ ነው ብለዋል። ተረጂነት ባርነትን ስለሚወልድ ማስቀረት ይገባናልም ነው ያሉት። ሊያጋጥሙ ለሚችሉ ሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች የራሳችንን ዐቅም መገንባት አለብን ሲሉም በአፅንኦት ገልፀዋል። የተሟላ ሀገራዊ ሉዓላዊነትን ከውስጥ ወደ ውጭ እያረጋገጡ መጓዝ ያስፈልጋልም ነው ያሉት።