ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትና የአየር መንገዱን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉ ናቸው
Jun 4, 2026 981
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2018(ኢዜአ)፦ ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትና የኢትዮጵያ አየር መንገድን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉ መሆናቸውን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሠላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 23ኛ መደበኛ ስብሰባው የተለያዩ አዋጆችን መርምሮ አጽድቋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ (ዶ/ር)፤ ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች እና የአየር መንገዱን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉ ናቸው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከሴራሊዮን ሪፐብሊክ፣ ከአንጎላ ሪፐብሊክ፣ ከባንግላዲሽ ሕዝባዊ ሪፐብሊክ እና ከኢስዋቲኒ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ጋር ያደረገቻቸውን የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ ሪፖርቶችና የውሳኔ ሃሳቦችን ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። እነዚህ የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆች ለንግድና ኢንቨስትመንት፣ ለቱሪዝም፣ ለዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች እንዲሁም የአየር ትራንስፖርት መዳረሻዎችን ለማስፋፋት ያላቸውን ከፍተኛ ጠቀሜታ አብራርተዋል። በተጨማሪም ስምምነቶቹ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም የሚያስጠብቁና በዘርፉ ያላትን ሚና በማጉላት ተጠቃሚነቷን የሚያሳድጉ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። ምክር ቤቱም በቀረቡት ረቂቅ አዋጆች ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ አዋጆቹን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። ከምክር ቤቱ አባላት በኩልም የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆቹ የአየር መንገዱን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ጉልህ ሚና እንደሚኖራቸው ተገልጿል። በሌላ በኩል፣ በኢትዮጵያ እና በሩሲያ ፌዴሬሽን መካከል የጋራ የባዮሎጂ ምርምር ማዕከል ለማቋቋም የተፈረመው ስምምነት ረቂቅ አዋጅም በምክር ቤቱ ጸድቋል። የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ (ዶ/ር)፤ ስምምነቱ የሀገሪቱን ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ዕድገት ለማፋጠን፣ ለዓሳ ሀብት ልማት፣ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን ለማሳደግና በዘርፉ የግል ባለሀብቶችን ለመሳብ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። በተጨማሪም የከፍተኛ ትምህርትና የምርምር ተቋማትን አቅም ለማሳደግና የምርምር ሥራዎችን ወደ ገበያ አውጥቶ ለማቅረብ ያለውን ጠቀሜታም አንስተዋል። በተጨማሪም ምክር ቤቱ በኢትዮጵያ እና በቬትናም ሶሻሊስት ሪፐብሊክ መንግሥት መካከል የዲፕሎማቲክ ወይም ኦፊሻል የአገልግሎት ፓስፖርት ለያዙ ዜጎች ቪዛን ለማስቀረት በተፈረመው የስምምነት ረቂቅ አዋጅ ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ፣ አዋጁን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል።
ስምምነቱ የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል ነው
Jun 4, 2026 363
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያና በአፍሪካ ልማት ባንክ መካከል የተፈረመው ስምምነት የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን በ23ኛ መደበኛ ስብሰባው የተለያዩ አዋጆችን መርምሮ አጽድቋል። በምክር ቤቱ የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) በኢትዮጵያና በአፍሪካ ልማት ባንክ መካከል የተፈረመው የአርብቶ አደሮች የኑሮ ዘይቤ ማሻሻያ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውል የብድር ስምምነት እና በኢትዮጵያና በዓለም አቀፍ የልማት ማህበር 6ኛው ምዕራፍ የልማታዊ ሴፍትኔት ማስፈጸሚያ ፕሮጀክት የተደረገ የብድር ስምምነት ረቂቅ አዋጆችን አስፈላጊነት በተመለከተ ለምክር ቤቱ ማብራሪያ አቅርበዋል። የአርብቶ አደሮች የምግብና የኑሮ ዘይቤ ማሻሻያ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውለው የብድር ስምምነት ከኢትዮጵያ የብድር ስትራቴጂ ጋር የሚጣጣም ነው ብለዋል። ስምምነቱ የአርብቶ አደሮችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ፣ ለግብርና፣ ለመስኖ ልማት፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋምና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ለውሃ መሰረተ ልማት፣ ለእንስሳት ጤና አገልግሎት፣ ለዘላቂ የመሬት አያያዝ፣ ለአየር ትንበያ ጣቢያዎችና ለሌሎች መሰረተ ልማቶች ማስፋፊያ እንደሚውልም ጠቅሰዋል። ምክር ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ ረቂቅ አዋጁን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። በሌላ በኩል በኢትዮጵያና በዓለምአቀፍ የልማት ማህበር 6ኛው ምዕራፍ የልማታዊ ሴፍትኔት ማስፈጸሚያ ፕሮጀክት የተደረገው የብድር ስምምነት ሴቶችና ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም በኑሮ ማሻሻል፣ በምግብ ዋስትና እና በማህበራዊ ጥበቃ ሰርዓት እየተከናወኑ ካሉ ብሔራዊ የልማት ፕሮጀክቶች ጋር የተናበበ በመሆኑ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። የምክር ቤቱ አባላት የብድር ስምምነቶቹ በግብርና፣ በመስኖ ልማት፣ በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋምና የአደጋ ተጋላጭነትን በመቀነስ የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል የተጀመሩ ሥራዎችን እንደሚያጠናክሩ ጠቁመዋል። ስምምነቶቹ በአግባቡ እንዲተገበሩና የታለመውን ግብ እንዲያሳኩ ድጋፍና ክትትል ማድረግ እንደሚገባም ተናግረዋል። ምክር ቤቱ የስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ በዝርዝር በመወያየት በአብላጫ ድምጽ አጽድቋቸዋል። በሌላ በኩል የፌዴራል ታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅን፣ የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅን፣ የምግብ ስርዓትና ስርዓተ ምግብ ረቂቅ አዋጅን፣ የኢትዮጵያ የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅን እና የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ ረቂቅ አዋጆች ቀርበው ውይይት ከተደረገባቸው በኋላ ለሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴዎች ተመርተዋል።
በበጀት ዓመቱ የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የተጀመሩ ተግባራትን ለማጠናቀቅ በትኩረት ይሰራል
Jun 4, 2026 358
አዲስ አበባ፤ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ)፦በ2018 በጀት ዓመት የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የተጀመሩ ተግባራትን ለማጠናቀቅ በትኩረት ይሰራል ሲሉ በብልፅግና ፓርቲ የሀረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሀላፊ አቶ ጌቱ ወዬሳ ገለጹ። በሀረሪ ክልል በ2018 በጀት ዓመት ቀሪ ጊዜያት በሚከናወኑ ተግባራት ላይ ውይይት ተደርጓል። በብልፅግና ፓርቲ የሀረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሀላፊ አቶ ጌቱ ወዬሳ በውይይቱ ላይ እንደገለፁት፥ የበጀት ዓመቱ ቀጣይ እቅዶችን በስኬት ለማጠናቀቅ በትኩረት ይሰራል። በመሆኑም ተቋማት የማህበረሰቡን የመልካም አስተዳደርና ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የጀመሯቸውን ተግባራት በቀሪ ጊዜያት ለማጠናቀቅ በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ ገልፀዋል። በተለይም በቱሪዝም ልማት፣የትምህርትና የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነትና በኮሪደር ልማት ላይ የተመዘገቡ አበረታች ውጤቶችን አጠናክሮ ማስቀጠል ልዩ ትኩረት እንደሚሰጠው ገልፀዋል። የሌማት ትሩፋት እና የከተማ ግብርና ስራዎችን በማጠናከር የግብርና ምርትና ምርታማነትን የማሳደጉ ስራም በበጀት ዓመቱ በልዩ ትኩረት ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆናቸውን አስገንዝበዋል። ለዜጎች የስራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት በመስጠት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው እንዲጎለብት ለማድረግ በቀጣይ ርብርብ እንደሚደረግም ገልፀዋል።
የባህርዳር ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከጣና ውበት ጋር በማሰናሰል የተገነባ ዘመን ተሻጋሪ የቱሪዝም ሃብት ነው
Jun 4, 2026 368
ባህር ዳር ፤ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ) ፡-የባህርዳር ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከጣና ውበት ጋር በማሰናሰል የተገነባ ዘመን ተሻጋሪ የቱሪዝም ሃብት መሆኑን የከተማዋ ነዋሪዎች ተናገሩ። ከተማዋ በተፈጥሮ የታደለችና አባይና ጣናን ተንተርሳ መመስረቷ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች ይበልጥ ውበቷ እየተገለጠ እንድትመጣ አድርጓታል። የከተማዋ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ትዕግስት አበጀ፤ ባህር ዳር ከተማ በተፈጥሮ የታደለች መሆኗን ተከትሎ ባለፉት ጥቂት አመታት ደግሞ ውበቷን የገለጡ የልማት ስራዎች መከናወናቸው ውበቷን ያጎላው መሆኑን ገልጸዋል። በከተማዋ ከኮሪደር ልማቱ በተጨማሪ የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ በርካታ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን አንስተው ውበቷና ድምቀቷ ይበልጥ እየጨመረ መጥቷል ብለዋል። የባህር ዳር የኮሪደር ልማት ከጣና ሃይቅ ጋር በተሳሰረ መልኩ የተገነባ መሆኑም ከተማዋን ልዩ ገፅታ ስለማጎናፀፉ አንስተዋል። እንደ አጠቃላይ የባህርዳር ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከጣና ውበት ጋር በማሰናሰል የተገነባ ዘመን ተሻጋሪ የቱሪዝም ሃብት መሆኑን ገልጸዋል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ ወጣት ደጀኔ አለምነው፤ የባህር ዳር ውበትና የቱሪዝም መስህብነት ከእለት ወደ እለት እያደገ መሆኑን ተናግሯል። በከተማዋ የኮሪደር ልማቱን ተከትሎ የተለያዩ የመዝናኛ ስፍራዎች፣ የአረንጓዴ ልማት፣ የእግረኛ፣ የሳይክል መንገዶችና ዘመናዊ የመንገድ ዳር መብራቶች መዘጋጀታቸው ከተማዋን ለነዋሪዎችና ለቱሪስቶች ምቹ አድርጓታል ብሏል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ገብረስላሴ ሳህሌ፤ ከባህር ዳር ከተማ ለዘመናት ተከልሎ የነበረው የጣና ሃይቅ ውበት በኮሪደር ልማት መገለጡ ለነዋሪዎችም ይሁን ለጎብኝው ደስታ ፈጥሯል ብለዋል። አሁን ላይ ወደ ባህር ዳር ጎራ የሚል ሁሉ ከተማዋን እየጎበኙ የጣናን ውበት እያደነቁ የሚደሰቱበት ስለመሆኑ ተናግረዋል። ባለፉት ጥቂት ዓመታት በባህር ዳር የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎችም የተገነቡ ሰው ተኮር የልማት ስራዎች የሚደነቁ ናቸው ብለዋል።
ምክር ቤቱ የአየር አገልግሎት ረቂቅ አዋጆችን መርምሮ አጸደቀ
Jun 4, 2026 227
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ)፡- የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 23ኛ መደበኛ ስብሰባ ኢትዮጵያ ከተለያዩ ሀገራት ጋር ያደረገቻቸውን የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆች መርምሮ አጸደቀ። የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማሕዲ (ዶ/ር) የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆችን ሪፖርትና የውሳኔ ሐሳቦች ለምክር ቤቱ አቅርበዋል፡፡ በዚሁ ወቅትም፤የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆቹ ኢንቨስትመንትን በመሳብና የአየር ትራንስፖርት መዳረሻዎችን በማስፋት ለሀገራችን የአየር ትራንስፖርትና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ያላቸው ሚና ወሳኝ ነው ብለዋል። ከአየር አገልግሎት ስምምነቶቹ መካከልም በኢትዮጵያ መንግሥትና እና በሴራሊዮን መንግሥት በኩል የተፈረመው አንዱ መሆኑን ጠቁመው፤ ስምምነቱ ለአየር መንገዶች ወደ ተመረጡ መዳረሻዎች በቀጥታ ለማረፍና ምቹ የአቪዬሽን አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚያስችል አስገንዝበዋል። ይህን የአየር አገልግሎት ረቂቅ አዋጅም፤ ምክር ቤቱ አዋጅ ቁጥር 1417 /2018 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡ በተመሳሳይ በአንጎላ ሪፐብሊክ እና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከል የተፈረመው የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጅ ለምክር ቤቱ የቀረበ ሲሆን፤ ስምምነቱ በሀገራቱ መካከል ያለውን በርካታ ዓመታት ያስቆጠረ ግንኙነት ለማሳደግ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መረጃ እንዳመላከተው፤ ይህ ረቂቅ አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1418 /2018 ሆኖ በሙሉ ድምጽ ፀድቋል። በሌላ በኩል በኢትዮጵያ መንግሥት እና በባንግላዴሽ መካከል የተደረገው የአየር አገልግሎት ስምምነት በሀገራቱ መካከል እያደገ የመጣውን የአየር ትራንስፖርት ፍሰት ከግምት ያስገባ መሆኑንም ነው ያነሱት። አክለውም፤ የውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ለመሳብ፣ በንግድ፣ ቱሪዝም እና የውጪ ምንዛሬ ለሀገራችን በማስገኘት ረገድ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል፡፡ በዚህም መሠረት ምክር ቤቱ ይህን ረቂቅ አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1419/ 2018 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡ ሌላው በምክር ቤቱ የጸደቀው የአየር አገልግሎት ረቂቅ አዋጅ፤ በኢትዮጵያ መንግሥት እና በኢስዋቲኒ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት መካከል የተደረገው ስምምነት ነው። ይህም ያለ በረራ ድግግሞሽ ገደብ የጭነት በረራዎችን ማከናወንን ጨምሮ ለበረራ የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶችን ከጉምሩክ ቀረጥ ነፃ ማስገባትን የሚያካትት በመሆኑ፤ የበረራ ወጪን እንደሚቀንስ አስረድተዋል። በተመሳሳይ ምክር ቤቱ ይህን ረቂቅ አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1420/2018 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡ የአየር አገልግሎት ስምምነቶቹ፤ የኢትዮጵያን ጥቅም የሚያስጠብቁና በዘርፉ በቀጣናው ያላትን ሚና በማጉላት ተጠቃሚነቷን የሚያሳድጉ መሆናቸው ተመላክቷል።
በክልሉ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግ ስራ እየተከናወነ ነው
Jun 4, 2026 268
ጋምቤላ፤ ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል የቡና አብቃይ ወረዳዎች የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የጋምቤላ ክልል ለግብርና ኢንቨስትመንትና ለተለያዩ ሰብሎች ልማት ምቹ የአየር ንብረትና ሰፊ ለም መሬት ካላቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች አንዱ ቢሆንም፣ የቡና ልማት ዘርፉ ግን ካለው ከፍተኛ እምቅ አቅም አንጻር በተገቢው ሳይለማ ለረጅም ዓመታት ቆይቷል። በተለይም እንደ ጋዶ፣ የጎደሬ ወረዳን ጨምሮ አንዳንድ የምዕራብ አኙዋክ አካባቢዎች ለቡና ልማት እጅግ ተስማሚ የተፈጥሮ ስነ-ምህዳር አለው። በእነዚህ ወረዳዎች የተራቆቱ አካባቢዎችን ከአረንጓዴ አሻራ ልማት ጋር በማቀናጀት በቡናና ጥምር የጥላ ዛፍ በመሸፈን ስነ-ምህዳርን በማሻሻልና የዘርፉን ምርታማነት በመጨመር ረገድ ውጤታማ ስራዎች እየተከናወኑ ነው። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንድሮው ቱት ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ በማጃንግ ዞን በሚገኙ የመንጌሽና የጎደሬ ቡና አብቃይ ወረዳዎች የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ተደራሽ በማድረግ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው። የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ ነባር ዝርያዎችን በተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች በመተካትና በተራቆቱ አካባቢዎች የቡና ጥምር ደን ልማትን በማስፋት ምርታማነትን የማሳደግ ስራ እንደሚከናወን ነው የገለጹት። በዘንድሮው ክረምት ከአረንጓዴ አሻራ ልማቱ ጋር በማቀናጀት በፕሮጀክቶች፣ በባለሃብቶችና በአርሶ አደሮች ከ4 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞች መዘጋጀታቸውን አቶ አንድሮው ተናግረዋል። በቢሮው የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ ሀብታሙ ገዳሙ እንዳሉት የተሻሸሉ የቡና ዝርያዎችን ከቴፒና ከጅማ ግብርና ምርምር ተቋማት በማምጣት ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግ ተግባር እየተከናወነ ነው። በምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራሙ ባለፉት ሁለት ዓመታት በተለይም በጎደሬ ወረዳ በሞዴል አርሶ አደሮች በኩታ ገጠም የቡና ማሳና በሰርቶ ማሳያዎች የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን የማስፋትና የማስተዋወቅ ስራ ሲከናወን መቆየቱን ገልጸዋል። በዘንድሮው ክረምትም ከ250 ሺህ የሚበልጡ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በኩታ ገጠም ለሚያለሙና ለሌሎች ሞዴል አርሶ አደሮች ለማሰራጨት ችግኞቹ መዘጋጀታቸውን አቶ ሀብታሙ ተናግረዋል። በማጃንግ ዞን ጎደሬ ወረዳ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች ካገኙ አርሶ አደሮች መካከል አቶ ዝናቤ ቢለው በሰጡት አስተያየት በተራቆቱ አካባቢዎች የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ከጥምር የደን ዛፍ ጋር አቀናጅቶ በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም በተመሳሳይ መልኩ የቡና ጥምር ደን ልማቱን በማስፋትና ተጠቃሚ ለመሆን እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም ድጋፍ የተራቆቱ አካባቢዎችን በቡናና በጥምር የጥላ ዛፍ በማልማት አካባቢውን ወደ ነበረበት በመመለስና ከዘርፉም ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ ሌላው የዚሁ ቀበሌ አርሶ አደር አቶ ከድር ሙሀመድ ናቸው።
በአሶሳ ከተማ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት የከተማዋን እንቅስቃሴ አቀላጥፏል
Jun 4, 2026 260
አሶሳ፤ ግንቦት 27/2018(ኢዜአ)፦ በአሶሳ ከተማ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት የከተማዋን የትራፊክ ፍሰትና አጠቃላይ እንቅስቃሴ ለማቀላጠፍ ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የከተማዋ ነዋሪዎች ተናገሩ። በአሶሳ ከተማ እየተካሄደ ያለው የኮሪደር ልማት፤ የከተማዋን መሠረተ ልማት ለማዘመን፣ የነዋሪዎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻልና ከተማዋን ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ሳቢ ለማድረግ ታስቦ የተጀመረ ሰፊ መርሃ ግብር ነው። በአንደኛው ዙር የተከናወኑት ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን ተከትሎ፣ አሁን ላይ ትኩረቱን የንግድና ማህበራዊ አገልግሎት ማዕከላትን ማዘመን ላይ ያደረገው ሁለተኛው ዙር ስራ በስፋት እየተገነባ ይገኛል። የሁለተኛው ዙር የኮሪደር ልማት፣ ዘመናዊ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ብቻ ሳይሆን ምቹ የእግረኛና የተሽከርካሪ መንገዶችንም በማካተት የከተማዋን ገጽታ እየቀየረ ይገኛል። አስተያየታቸውን የሰጡን የከተማዋ ነዋሪዎች እንደገለጹት፣ የእግረኛ እና የተሽከርካሪ መንገዱ ተለይቶ መሰራቱ የትራፊክ ፍሰቱን በእጅጉ አቅልሎታል። ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል አቶ ማስረሻው አራጌ እንዳሉት፣ ከዚህ ቀደም የነበረው መንገድ ጠባብ ከመሆኑ የተነሳ ለተሽከርካሪም ሆነ ለእግረኞች ምቹ እንዳልነበር አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት ግን በኮሪደር ልማቱ ለሁሉም ምቹ መንገድ በመፈጠሩ፣ የትራፊክ እንቅስቃሴው መሳለጡን አቶ ማስረሻው ተናግረዋል። ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ የሺወርቅ ንብረት፤ የኮሪደር ልማቱ ከተማዋን በሁሉም መስክ ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትሆን አድርጓታል ብለዋል። በተለይም በሁለተኛው ዙር እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት፣ በእግረኞች ላይ ይደርስ የነበረውን የትራፊክ አደጋ በመቀነስ ረገድ አይነተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። በከተማዋ የባጃጅ አሽከርካሪ የሆነው አህመድ ሰኢድ በበኩሉ የኮሪደር ልማቱ ለአሸከርካሪዎች ነፃነትን የሰጠ እና ለተሽከርካሪዎችም ምቹ መሆኑን ተናግሯል። የኮሪደር ልማቱ ለአሸከርካሪዎች እና እግረኞች የፈጠረው ምቹ ሁኔታ የትራፊክ አደጋን ከመቀነስ አንፃር ትልቅ ትርጉም አለው ያሉት ደግሞ በአሶሳ ከተማ የትራፊክ ተቆጣጣሪ ምክትል ሳጅን ኢዘዲን አልበሽር ናቸው። የኮሪደር ልማቱ የትራፊክ ተቆጣጣሪዎችን የሥራ ጫና የቀነሰ እና የተቀላጠፈ የትራፊክ እንቅሰቃሴ እንዲፈጠር አይነተኛ ሚና ያበረከተ መሆኑን ጠቁመዋል።
የሚያዝያ እና ግንቦት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቁልፍ ተግባራት ቅኝት ከምስል ጋር!
Jun 3, 2026 797
የኢንዱስትሪ መስፋፋት እና ኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነት:- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ነጻነት ለማረጋገጥ፣ የረጅም ጊዜ የኢንዱስትሪ እድገትን እና ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካትን መሰረት ያደረጉ የተለያዩ የአምራች ዘርፉ እንቅስቃሴዎችን በንቃት መርተዋል፤ በዚህም የፋይናንስ አቅርቦትን ማሳደግ ላይ ያተኮረውን 4ኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ በይፋ የከፈቱ ሲሆን፣ የወጣቶችን የስራ እድል ለማስፋፋትም በአዲስ ኣበባ የሚገኘውን የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ መርቀው ከፍተዋል። በተጨማሪም የታዳሽ ሃይል አቅምን ለማሳደግ አዲስ ስራ የጀመረውን የጎበዜ የሶላር ሴል ማምረቻ ፋብሪካን እንዲሁም፣ የአካባቢውን ጥሬ እቃዎች በመጠቀም የገቢ ምርቶችን ለመተካት ያለመውን በሞጆ ከተማ የሚገኘውን የግራንደር የሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካንም መርቀው ከፍተዋል። የላቀ የጤና ስርዐትና ዘመናዊ አገልግሎቶች:- ኢትዮጵያ በልዩና በላቀ የህክምና ብቃት ቀጣናዊ ማዕከል ለመሆን የምታደርገውን ስትራቴጂካዊ ጉዞ ግብ ለማሳካት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እጅግ በዘመኑ የህክምና ቴክኖሎጂዎች እና በሮቦቲክስ የታገዘውን እንዲሁም የካንሰር እና የልብና ህመሞችን በሀገር ውስጥ ለማከም የተገነባው ዘመናዊውን የላፍቶ ሆስፒታል በአዲስ አበባ በይፋ መርቀው ከፍተዋል፤ በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ የህክምና ስልጠና ላይ ለሚገኙ የሩዋንዳ እና ከሌሎች አፍሪካ ሀገራት ለመጡ የህክምና ባለሙያዎች ይፋዊ የእራት ግብዣ አድርገዋል። መሰረተ ልማት፣ ዘላቂ አገልግሎቶች እና ትራንስፖርት:- ጠቅላይ ሚኒስትሩ የንግድና ማህበራዊ ትስስርን የሚጠናክረውንና የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የአገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውን አዲሱን የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ መርቀዋል፤ በተጨማሪም በጎመሌ ወረዳ የሚገኘውን የደሴ ጎራ ግድብን ጨምሮ የፊና ኦሮሚያ መስኖ ፕሮጀክቶች መጠናቀቃቸውን የተከታተሉ ሲሆን ንጹህ ውሃ ለማቅረብና ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ የድርቅ መቋቋም አቅምን ለመገንባት የተነደፈውን መጠነ-ሰፊ የቦረና የውሃ አቅርቦት ፕሮጀክት ማስፋፊያ ስራ ጉብኝትንም በበላይነት መርተዋል። የግብርና ትራንስፎርሜሽን እና የምግብ ሉዓላዊነት:- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የክላስተር እርሻን ለማስፋፋት በዋና ዋና የግብርና ክልሎች የመስክ ጉብኝት ያደረጉ ሲሆን በዚህም የሀገር ውስጥ የዩሪያ ማዳበሪያ ምርትን ለማሳደግ የታቀደውን የፋብሪካ ግንባታ ሂደት ለመገምገም ከአሊኮ ዳንጎቴ ጋር ወደ ጎዴ ተጉዘዋል። በተጨማሪም በምስራቅ ቦረና ዞን በሺዎች የሚቆጠሩ አባወራዎችና እማወራዎችን ያሳተፈውን መጠነ ሰፊ የክላስተር ግብርና ንቅናቄ የጎበኙ ሲሆን በሰሜን ሸዋ ዞን በብዙ ሄክታር መሬት ላይ የሚገኘውን የስንዴ እርሻ ልማትም ጎብኝተዋል። የሚዲያ እና የብሔራዊ ፖሊሲ ሉዓላዊነት:- የመንግሥት ተቋማትን እና የብሔራዊ ፖሊሲ ነጻነትን ለማጠናከር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀገራዊ የምክክር መድረኮች ላይ ተገኝተዋል። ዲጂታላይዝድ ወደሆነ እና ራሱን ወደቻለ የስታቲስቲክስ ማዕቀፍ የሚደረገውን ሀገራዊ ሽግግር ለመደገፍ "የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነጻነት" በሚል መሪ ቃል በተዘጋጀው ብሔራዊ ጉባኤ ላይ የተገኙ ሲሆን፤ በተጨማሪም የብሔራዊ ምክክር ኮሚሽን ወደ ትግበራ ምዕራፍ ሊሸጋገር የቀረበውን ይፋዊ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ተቀብለዋል። በዚሁ ወር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለብሔራዊ ልማት የሚረዱ የሚዲያ ስነ-ምግባር ሙያዊ መመሪያዎችን አስምረው የተናገሩበት እና “የሚዲያ እመርታ ለሀገር ግንባታ” በተሰኘው ብሔራዊ መድረክ ላይ ለሚዲያ ዘርፍ መሪዎች እና ባለሙያዎች ንግግር አድርገዋል። የባህል ጥበቃ እና አከባቢያዊ እንክብካቤ:- በኦሮሚያ ክልል የገዳ ሥርዓት ታሪክንና ፍልስፍናን ለመጠበቅ በያቤሎ ከተማ የተገነባውን የቦረና ባህል ማዕከል ጠቅላይ ሚኒስትሩ መርቀው የከፈቱ ሲሆን ማዕከሉ በመደመር መጽሐፍ ሽያጭ ገቢ የተደገፈ እንደሆነም ይታወሳል። ከዚህ ጎን ለጎን፣ የዱር እንስሳትና ብዝሃ-ሕይወት መጠበቂያ ሆኖ የሚያገለግለውን የቦረና ብሔራዊ ፓርክ መርቀው ከፍተዋል። ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ እና የሁለትዮሽ ግንኙነቶችን የሚያጠናክሩ ማዕቀፎች:- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ አጋርነት ለማጠናከር በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ከፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር የተወያዩ ሲሆን በብድር እና ተለያዩ ዘርፎች አጋርነት ላይ ስምምነቶችን አድርገዋል። በተጨማሪም በናይሮቢው አፍሪካ ፎርዋርድ ጉባኤ ላይ የተሳተፉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ከተገበረቻቸው የልማት ሞዴሎች ልምድ ከማካፈላቸውም ባለፈ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክሪስታሊና ጆርጂየቫ ጋር የኢኮኖሚ ምክክር አድርገዋል። በዚሁ ወር በጅቡቲ የፕሬዚዳንት እስማኤል ዑመር ጌሌን በዓለ-ሲመት የታደሙ ሲሆን ከኔዘርላንድስ ጠቅላይ ሚኒስትር ሮብ ዬተን ጋር የስልክ ውይይት አድርገዋል። በመጨረሻም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት 80ኛ ዓመት መታሰቢያ ምክንያት በማድረግ የቴምብር ስብስብ ይፋ አድርገዋል።
በሐረሪ ክልል 11 ሺህ 956 ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ ነው
Jun 3, 2026 627
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በበልግ እና መኸር እርሻ በድምሩ 11 ሺህ 956 ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታውቋል። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የግብርና ልማት ቢሮ ኃላፊ ሮዛ ኡመር እንደገለፁት በክልሉ ያለውን አነስተኛ መሬት በአግባቡ ተጠቅሞ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀናጀ ስራ እየተሰራ ይገኛል። በክልሉ በ2018/19 በበልግ እና መኸር እርሻ በድምሩ 11 ሺህ 956 ሄክታር መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ለማልማት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በበልግ ዝናብ እስካሁን 8 ሺህ 681 ሄክታር መሬት በዘር መሸፈኑን ጠቁመው፥ ቀሪው 3 ሺህ 275 ሄክታር በክረምት መኽር ዝናብ ቶሎ ደራሽ ማሽላ እና ስንዴ ለመዝራት አሰፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። በክልሉ ሶስት የገጠር ወረዳዎች በሚገኙ ማሳዎች ላይ እየለሙ የሚገኙት ሰብሎችም ማሽላ፣ በቆሎ እና ስንዴ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ለመኸር እርሻው ምርትና ምርታማነት ማደግ አስፈላጊው የማዳበሪያ፣ የዘርና ሌሎች የግብርና ግብዓት አቅርቦት ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ያመለከቱት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሯ በምርት ዘመኑ እየለሙ ካሉ ሰብሎች 300 ሺህ ኩንታል ምርት ለመሰበሰብ መታቀዱንም አስረድተዋል። በየደረጃው ያሉ የግብርና ባለሙያዎችም ለአርሶ አደሩ አስፈላጊውን ሙያዊ እገዛና ድጋፍ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም አርሶ አደሩን ከዝናብ ጠባቂነት ከማላቀቅና ተጠቃሚነትን ከማሳደግ አንፃር አበረታች ስራዎች ተከናውነዋል ነው ያሉት። በቀጣይም የተገኙ አበረታች ውጤቶችን በማስቀጠል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማጎልበትና ምርት እና ምርታማነትን ለማሳደግ የላቀ ትኩረት እንደሚሰጥ ገልጸዋል።
የሀገር ሉዓላዊነትና ነጻነት በምልዐት የሚረጋገጠው በጥራት፣ በዓይነት እና በብዛት የኢንዱስትሪ ምርቶችን ማምረት ስንችል ነው
Jun 3, 2026 625
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 26/2018(ኢዜአ)፦የሀገር ሉዓላዊነትና ነጻነት በምልዐት የሚረጋገጠው በጥራት፣ በዓይነት እና በብዛት የኢንዱስትሪ ምርቶችን በራስ ዕውቀት፣ በራስ ክህሎት እና በራስ ቴክኖሎጂ ማምረት ስንችል ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤የሀገር ሉዓላዊነትና ነጻነት በምልዐት የሚረጋገጠው በጥራት፣ በዓይነት እና በብዛት የኢንዱስትሪ ምርቶችን በራስ ዕውቀት፣ በራስ ክህሎት እና በራስ ቴክኖሎጂ ማምረት ስንችል ነው ብለዋል፡፡ መንግሥትም በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ የታለመውን ዘላቂ ዕድገት እና ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ ፖሊሲዎችን ማሻሻሉን፡ አሠራሮችን መዘርጋቱን እና ማበረታቻዎችን ማድረጉን ገልጸዋል። የዚህ ሪፎርም አካል የሆነው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄም ፍሬው በግልጽ እየታየ መሆኑን ጠቁመዋል።
በምርጫው ሂደት ለዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በልማትም እናስቀጥላለን
Jun 3, 2026 481
ድሬዳዋ፤ ግንቦት 26/2018(ኢዜአ)፦ በምርጫው ሂደት ለዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በልማትም እናስቀጥላለን ሲሉ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የድሬዳዋ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። በሀገር አቀፍ ደረጃ ግንቦት 24 በተካሄደው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ዜጎች የማለዳው ቅዝቃዜና የምሽቱ ጨለማ ሳይበግራቸው ድምፃቸውን ሰጥተዋል። የምርጫውን ሂደትና የነበረውን ተሳትፎ በማስመልከት የኢዜአ ሪፖርተር በድሬዳዋ ከተማ ተዘዋውሮ ነዋሪዎችን አነጋግሯል። ነዋሪዎቹ በሰጡት አስተያየት በምርጫው ሂደት ለዴሞክራሲ እውን መሆን ያበረከቱትን አስተዋፅኦ፣ በከተማዋ የልማትና የዕድገት ጉዞ ላይ ለማስቀጠል እንደሚተጉ ገልጸዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ ምንዳ ሰለሞን እና ወይዘሮ ማህሌት ታደለ፤ በድምፅ አሰጣጡ የነበራቸው ተሳትፎ ለራሳቸውና ለልጆቻቸው የምትመች ሀገር የመገንባት ሃላፊነት መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም በምርጫው ሂደት ለዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በልማትም እናስቀጥላለን ነው ያሉት። አቶ አለማየሁ በቀለ፣ ወይዘሮ ከድራ ኡስማን እና አቶ ግርማ በዛዬ በበኩላቸው፤ በታሪካዊው ምርጫ መሳተፍና ድምፅ መስጠት ሀገራዊ ሃላፊነት መሆኑን አንስተው፤ የምርጫ ሂደቱ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ በጥሩ መሰረት ላይ የሚያኖር መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም በምርጫው ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በቀጣይ የሀገር ልማትና የሰላም ግንባታ ሂደት ላይ ለማስቀጠል ዝግጁ ነን ብለዋል።
በዞኑ ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በተከናወነ የንብ ማነብ ስራ ወደ 3 ሚሊዮን ኪሎ ግራም የሚጠጋ የማር ምርት ተገኘ
Jun 3, 2026 266
ደብረ ማርቆስ ፤ግንቦት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በተከናወነ የንብ ማነብ ስራ ወደ 3 ሚሊዮን ኪሎ ግራም የሚጠጋ የማር ምርት ማግኘት መቻሉን የዞኑ እንስሳትና ዓሳ ሃብት መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የንብና ሃር ልማት ባለሙያ አቶ ስማቸው ዳምጤ ለኢዜአ እንደገለጹት በዞኑ የሚገኙ አርሶ አደሮችን ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በንብ ማነብ ስራ በማሳተፍ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተሰራ ነው። በበጀት ዓመቱ በማነብ ስራ የተሰማሩ አርሶ አደሮችን በመደገፍና በማበረታታት ከ2 ነጥብ 1 ሚሊዮን ኪሎ ግራም በላይ ማር ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል። በዞኑ የሚገኙ ከ48 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ባሏቸው ከ200 ሺህ በላይ የንብ ቀፎዎች እስካሁን ከ2 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኪሎ ግራም በላይ ማር ማምረት መቻሉን ተናግረዋል። የተመረተውን ማር ለገበያ በማቅረብ ከ1 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘት መቻሉን ገልጸዋል። ምርቱም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ1 ሚሊዮን ኪሎ ግራም በላይ ብልጫ እንዳለው ጠቁመው ለዚህም የተስተካከለ ዝናብ መኖር ለዕፅዋት ማበብ ምክንያት በመሆኑ ምርቱ ሊጨምር መቻሉን አስረድተዋል። ይህም ከአንድ ዘመናዊ ቀፎ በአማካኝ 30 ኪሎ ግራም፣ ከሽግግር ቀፎ 18 ኪሎ ግራምና ከባህላዊ ቀፎ ስምንት ኪሎ ግራም ማር እንዲገኝ በማስቻሉ የመጣ ውጤት መሆኑንም አብራርተዋል። ከተሳታፊዎች መካከል የአዋበል ወረዳ የእነቢ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ጌታሁን ይግዛው፤ ከሰብል ልማቱ ጎን ለጎን በንብ ማነብ ስራ ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ ሆኛለሁ ብለዋል። በቅርብ ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ የለሙ አካባቢዎች ለንብ ማነብ ስራ ምቹ ሁኔታ በመፍጠራቸው ከ10 ዘመናዊና የሽግግር ቀፎዎች ከ190 ኪሎ ግራም በላይ ምርት ማግኘታቸውንም ተናግረዋል። የዚሁ ወረዳ የገሽ ቀበሌ ነዋሪ ወጣት ቢምረው አወቀ በበኩሉ ካሉት 13 ዘመናዊና የሽግግር የንብ ቀፎዎች ከ180 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘቱን ገልጿል።
በኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ስኬታማ አቅም እየተገነባ ነው
Jun 2, 2026 1119
አዲስ አበባ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ስኬታማ አቅም እየተገነባ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በፋይናንስ አቅርቦት የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማጠናከር የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። በሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ልማት ማበረታቻ የፋይናንስ አቅርቦት የትብብር ስምምነቱን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዝዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) ፈርመውታል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ የዜጎቿን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጥ የተቃና ጉዞ ላይ ናት ብለዋል። የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልፅግና ለማረጋገጥም የወጣቱን ዕምቅ የፈጠራ ሃሳብና አቅም ወደ ተግባር የሚለውጥ ውጤታማ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የተቋማት ትብብርም ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትን ያረጋገጠች ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመገንባት ጉልህ ሚና እንደሚጫወት አንስተዋል። የተቋማቱ የትብብር ስምምነትም የሥራ ፈጣሪ ወጣቶችን የፈጠራ ክህሎት የሚያዳብር የፋይናንስ አቅርቦት በማመቻቸት የነገ ተስፋቸውን ምቹ ምኅዳር የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል። ለአብነትም ኢትዮጵያ በሁሉም መስክ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ የአምራችነት ባህልን የሚገነባ አስቻይ ሁኔታ እየፈጠረች መሆኗን እንደሚያሳይ ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ስምምነቱ በተለያዩ ክልሎች በግብርና ዘርፍ ላይ የተሰማሩ ወጣቶችን የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት የሚያሳድግ ነው ብለዋል። የተቋማቱ ትብብር ስምምነትም የሴቶችና ወጣቶችን የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት አቅም በማሳደግ ከፍተኛ የወለድ መጠን ቅናሽ የተደረገበት መሆኑን ገልጸዋል። በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የግብርና ኢንተርፕራይዞች ልማት ለሥራ ዕድል ፈጠራ ፕሮጀክት አስተባባሪ አሽቅ በድሩ፤ ፕሮጀክቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚተገበርና የዜጎችን የግብርና ምርታማነት የሚያሻሽል የፋይናንስና የግብዓት አቅርቦት የሚያስገኝ ነው ብለዋል።
የምርጫ ንቁ ተሳትፏችንን በልማት ለመድገም ተዘጋጅተናል- የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዎች
Jun 2, 2026 689
ሃዋሳ ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በምርጫ ወቅት ያሳዩትን ንቁ ተሳትፎ በልማት ለመድገም መዘጋጀታቸውን የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ በከተማዋ የተለያዩ ምርጫ ጣቢያዎች ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት ተለጥፎ ለህዝብ ይፋ የተደረገ ሲሆን ህብረተሰቡም ውጤቶቹን እየተመለከተ ነው። ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቶችን ሲመለከቱ ኢዜአ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች በምርጫ ወቅት ያሳዩትን ንቁ ተሳትፎ በቀጣይ በልማት ሥራ እንደሚደግሙ ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል በከተማው የለኩ ቀበሌ ነዋሪው አቶ ታከለ ሱንደዶ እና የዳቶ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ቶማስ ፈልታሞ፤ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ላይ በንቃት መሳተፋቸው እንደሚያኮራቸው ገልጸዋል። አቶ ቶማስ ጨሬ እና አቶ ከበደ ዮናስ በበኩላቸው፤ ህዝብ የስልጣን ባለቤት መሆኑን ባረጋገጠበት ጠቅላላ ምርጫ ያሳዩትን ተሳትፎ በልማት እንደሚደግሙ አረጋግጠዋል። በሃዋሳ ምርጫ ክልል በ08 ምርጫ ጣቢያዎች ትናንት ድምጽ የተሰጠ ሲሆን የድምጽ ቆጠራ ተጠናቆ የተለጠፉ ጊዜያዊ ውጤቶችን ህዝቡ እየተመለከተ ነው፡፡
የሻሸመኔ ከተማ ነዋሪዎች በጠቅላላ ምርጫው ያሳዩትን ተሳትፎ በማስቀጠል ልማትን ለማፋጠን በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እንደሚወጡ ገለጹ
Jun 2, 2026 542
ሻሸመኔ ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በጠቅላላ ምርጫው ያሳዩትን ተሳትፎ በማስቀጠል ልማትን ለማፋጠን በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እንደሚወጡ የምዕራብ አርሲ ዞን የሻሸመኔ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። ነዋሪዎቹ ሂደቱን አስመልክተው ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ በህዝብ ድምጽ አሸናፊ ሆኖ ከሚመሰረተው መንግስት ጋር በመሆን ልማትን ለማስቀጠል መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። በምርጫው የታየው የሕዝብ ንቁ ተሳትፎን በማጎልበት ልማትን ለማጠናከር በሚደረገው ሂደት የድርሻቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውንም አክለዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡ የከተማዋ ነዋሪዎች መካከል የምዕራብ አርሲ ዞን አባ ገዳዎች ሰብሳቢ አባ ገዳ ነጌሶ ገመቹ፤ በጠቅላላ ምርጫው የታየውን የህዝቡን ጠንካራ ተሳትፎ በማስቀጠል ዴሞክራሲን ለማጎልበትና ልማትን ለማፋጠን በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል። የከተማው ነዋሪ ወይዘሮ ቀበኔ ደሶ፤ በጠቅላላ ምርጫው ህዝቡ ያሳየው ተሳትፎ የኢትዮጵያ ሕዝብ ለሰለጠነ ፖለቲካ ያለውን ዝግጁነትና መንግስት በህዝብ ይሁንታ ብቻ መመስረት እንዳለበት ያለውን ጽኑ ፍላጎት ያሳያል ብለዋል። ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ መሠረት ገብረማርያም በበኩላቸው፤ በድምጽ መስጠት ወቅት ያሳየነውን ንቁ ተሳትፎ ቀጣይ ልማትን በማፋጠን እንደግመዋለን ብለዋል።
በግብርና እና ሌሎች ዘርፎች የተሰማሩ ሴቶችና ወጣቶችን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jun 2, 2026 326
አዲስ አበባ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በግብርና እና ሌሎችም ዘርፎች የተሰማሩ ሴቶችና ወጣቶችን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ገለጹ፡፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በክህሎት ልማት፣ በሥራ ፈጠራ ማበረታቻ እና በፋይናንስ አቅርቦት ዙሪያ ያላቸውን የጋራ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል እና የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) ፈርመውታል። በመርሐ ግብሩ ላይ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል እንደገለጹት፤ የወጣቶችን ፍላጎት የተገነዘበ አገር የለውጥ ጉዞው የተቃና ይሆናል። የኢትዮጵን ሁለንተናዊ እድገትና የብልጽግና ጉዞ ስኬታማ ለማድረግ የወጣቱን እምቅ አቅምና የፈጠራ ሐሳቦች ማዕከል ያደረጉ ውጤታማ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዚህም የተቋማት በቅንጅት መሥራት ጠንካራ አገር ከመገንባት አኳያ ጉልህ ሚና እንደሚጫወትም አብራርተዋል። የሁለቱ ተቋማት ስምምነትም ለወጣቶችና ለሥራ ፈጣሪዎች የፋይናንስ አቅርቦትን በዘላቂነት በማቅርብ፣ የነገ ተስፋቸውን ለማለምለም ምቹ ምኅዳር የሚፈጥር መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ በተለይም የወጣቶችን በክህሎት የታገዙ የፈጠራ ሐሳቦች በፍጥነት ወደ ተግባርና ወደ አምራችነት እንዲቀየሩ ትልቅ ድልድይ እንደሚሆን ተናግረዋል። በተለያዩ አካባቢዎች ለሚገኙ ወጣቶች አነስተኛ መጠን ያለው ብድር እና የግብዓት አቅርቦት መስጠትን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ኢሳያስ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ስምምነቱ በተለያዩ ክልሎች በግብርና ዘርፍ ላይ ተሰማርተው ለሚገኙ ወጣቶች የገንዘብና የግብዓት አቅርቦት ማድረግን ያለመ መሆኑን ጠቅሰዋል። ይህንንም ተፈጻሚ ለማድረግ የፋይናንስ ተቋማቱ ቀደም ሲል ያቀርቡበት ከነበረው የወለድ መጠን ላይ ከፍተኛ ቅናሽ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል።
በጠቅላላ ምርጫው የታየው የህዝብ ተሳትፎ የልማት መነሳሳትን የሚያጠናክር ነው -የአዳማ ከተማ ነዋሪዎች
Jun 2, 2026 105
አዳማ ፤ግንቦት 25/2018 (ኢዜአ)፦በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የታየው የህዝብ ተሳትፎ የልማት መነሳሳትን እንደሚያጠናክር የአዳማ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። አስተያየት ሰጪዎቹ እንደተናገሩት፤ በምርጫው የታየው ተሳትፎ ለልማት እና ለእድገት በጎ አስተዋጽኦ ያለው ነው። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ሲስተር ዓለም ጀማል እንዳሉት፤ በጠቅላላ ምርጫው የታየው የህዝብ ተሳትፎ በትብብር እና በህብረት ሀገራችንን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ማሻገር እንደሚቻል ያሳየ ነው። በአዳማ ከተማ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ስራዎች እንዲቀጥሉ የበኩላቸውን እንደሚወጡም ገልጸዋል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ንጉሴ ኦብሴ፤ ህዝቡ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በሌሊት ብርድና በረጃጅም ሰልፎች ሳይበገር ያሳየው ጽናትና ቁርጠኝነት፣ ለልማት ያለውን መነሳሳት የሚያጠናክር ነው ብለዋል። ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎች እንዲቀጥሉ የሚጠበቅብኝን እወጣለሁ ብለዋል። አቶ ጌታቸው ወርቅነህ በበኩላቸው በምርጫው የታየው የህዝብ ተሳትፎ ህዝቡ ለሰላምና ለልማት ያለውን ተነሳሽነት በግልጽ ያሳየ መሆኑን ተናግረዋል። ወደ ፊትም አንድነታችንን በማጠናከር በልማት ስራዎች ላይ መረባረብ አለብን ብለዋል።
በምርጫው ላይ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በቀጣይ በጋራ ሀገር ለመገንባት ማዋል አለብን- የጅማ ከተማ ነዋሪዎች
Jun 2, 2026 226
ጅማ ፤ግንቦት 25/2018(ኢዜአ)፡- በምርጫው ላይ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በቀጣይ በጋራ ሀገር ለመገንባት ማዋል አለብን ሲሉ የጅማ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። በጅማ ከተማ ቆጠራ በተጠናቀቀባቸው የምርጫ ጣቢያዎች ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቶች እየተለጠፉ ሲሆን፣ ሕዝቡም እየተመለከተ ይገኛል። በጅማ ከተማ ባሉት 117 የምርጫ ጣቢያዎች ነዋሪዎች ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ ድምፃቸውን ሲሰጡ መዋላቸውን የጅማ ከተማ የምርጫ ክልል መግለጹ ይታወቃል። በከተማዋ ጊዜያዊ የምርጫ ውጤት ሲመለከቱ ኢዜአ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች፤ አጠቃላይ በምርጫ ሂደቱ በትናንትናው እለት ደግሞ ድምፅ ለመስጠት ከማለዳ እስከ ምሽት የነቃ ተሳትፎ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም በምርጫው ላይ ያሳየነውን ጠንካራ ተሳትፎ በቀጣይ በጋራ ሀገር ለመገንባት ማዋል አለብን ሲሉ አስተያየት ሰጭዎቹ ተናግረዋል። ትላንት ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ድምጻቸውን ሰጥተው፣ በማለዳ ውጤት ለማየት በምርጫ ጣቢያ የተገኙት አቶ አወል አብዱረህማን፤ ሀገርን መውደድ ከሚገለጽባቸው መንገዶች አንዱ በምርጫ መሳተፍ ነው ይላሉ። ሰላማዊ ምርጫ ተካሂዶ መጠናቀቁ የኢትዮጵያና የሕዝቦቿ ትልቅ ስኬት መሆኑን ገልጸው፤ በምርጫ ያሳየነውን ተሳትፎ በሌሎች የልማት ሥራዎችም መድገም አለብን ብለዋል። ከዚህም ባለፈ የምርጫ ውጤትን በፀጋ በመቀበል የዴሞክራሲ መሠረትን ማፅናትና የሀገርን ልማት ማፋጠን ይገባል ሲሉም ገልጸዋል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ አቶ በሽር አህመድ በበኩላቸው፣ በምርጫው የነቃ ተሳትፎ አድርገው መምረጣቸውን ገልጸው፤ በቀጣይም ሀገር በምትፈልገው መስክ ሁሉ የነቃ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ቀደም ሲል በተካሄዱ ምርጫዎች ላይ መሳተፋቸውን ያስታወሱት አቶ በሽር፤ ይህ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በርካታ ዜጎች የተሳተፉበትና ሰላማዊ መሆኑ በእጅጉ እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል። በመሆኑም በምርጫው የተሳተፉ አካላት ሁሉ ውጤቱን አምኖ በመቀበል የኢትዮጵያን ዕድገትና ሰላም ሊያስቀጥሉ እንደሚገባ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። በምርጫው ድምጿን በመስጠቷ ትልቅ ደስታ እንደተሰማት የገለጸችው ወይዘሮ ዘቢባ ጀማል በበኩሏ፣ ውጤቱን ለማየት በማለዳው በጊንጅ ጉድሩ ቀበሌ ገጠር ቴክኖሎጂ ምርጫ ጣቢያ መገኘቷን ተናግራለች። በቀጣይም በምርጫው ላይ ያደረጉትን ተሳትፎ ሀገር በምትፈልገው የልማት ሥራዎች ላይ ለመድገም ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል። በጅማ ከተማ የኢዜአ ሪፖርተር ተዘዋውሮ በተመለከታቸው በጊንጅ ጉድሩ ቀበሌ ገጠር ቴክኖሎጂ ምርጫ ጣቢያ፣ በውኃ ፍሳሽ ምርጫ ጣቢያ እና በሌሎችም ጣቢያዎች የምርጫ ውጤቶች በአሁኑ ሰዓት እየተለጠፉ ይገኛሉ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከእንጦጦ እስከ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ያለውን የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ስራ አስጀመሩ
Jun 2, 2026 315
አዲስ አበባ፤ግንቦት 25/2018(ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከእንጦጦ እስከ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ያለውን መልሶ ማልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት በይፋ ስራ አስጀምረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ከ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ማግስት፣ዛሬ ጠዋት ከእንጦጦ እስከ ቀጨኔ መድኃኔዓለም ያለውን የመልሶ ማልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት በይፋ ስራ አስጀምረናል ብለዋል። ይህ ትልቅ ተነሳሽነት፤የተራቆቱ አካባቢዎችን በዘመናዊ የአፈር ጥበቃ እና በወንዝ ማጣራት ወደ አረንጓዴ ስፍራዎች በመቀየር፣ የፍራፍሬ ፓርኮችን ከእግር ጉዞ እና ከብስክሌት መንገዶች ጋር በማቀናጀት መዲናችንን አድሷል ነው ያሉት። ፕሮጀክቱ በአጠቃላይ 22.25 ኪሎ ሜትር የወንዝ ዳርቻ ልማትን የሚሸፍን መሆኑን ገልጸው፥ይህ የማይቆራረጥ የልማት ስራችን ህያው ምስክር ከመሆኑም በላይ የሃገራዊ ዕድገታችን፣ የአካባቢ ጥበቃ እና የከተማ እድሳት በተግባር የታየበት ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ከተሞች የመሬት ይዞታ ካዳስተር ምዝገባ ሥርዓት የገቢ አቅማቸውን በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው
May 29, 2026 2106
አዲስ አበባ፤ግንቦት 21/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ከተሞች የመሬት ይዞታ ካዳስተር ምዝገባ ሥርዓት የከተሞችን የገቢ አቅም በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ፈንታ ደጀን ገለጹ። ከተሞች የገቢ አቅማቸውን በመጠቀም ብድር ማግኘት የሚችሉበትን ሥርዓት ለመዘርጋት እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ለኢዜአ እንዳሉት፤ ከተሞች ለአጠቃላይ ሀገራዊ ምርት ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው ናቸው። የኢትዮጵያ ከተሞች እስከ 58 በመቶ ለአጠቃላይ ሀገራዊ የምርት ድርሻ እያበረከቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ በኮሪደር፣ወንዝ ዳርቻና ዲጂታላይዜሽን የተከናወኑ ስኬታማ የልማት ተግባራት ስሉጥ ከተሞችን በመፍጠር ከፍተኛ ጠቀሜታ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊ የከተሜነት ምኅዳር የመፍጠር ሥራም ዜጎች ፈጣንና ቀልጣፋ የመንግሥት አገልግሎት የሚያገኙበት አስቻይ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን አንሰተዋል። የከተሞች ማዘጋጃ ቤታዊና የተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ ወደ ዲጂታል ሥርዓት መሸጋገሩም ፈጣንና ቀልጣፋ ምኅዳር መፍጠሩን አስረድተዋል። በተለይም በአንድ ማዕከል አገልግሎት ዜጎች የመንግሥት አገልግሎቶችን በተማከለ ሥርዓት በጥራትና ፍጥነት የሚያገኙበት ዕድል እንደፈጠረ ተናግረዋል። የከተሞችን የመሬት ይዞታ በፍትሐዊነት ለማስተዳደርም ምዝገባ እየተካሄደ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ 6 ነጥብ 6 ሚሊየን ፐርስል የከተማ መሬት ውስጥ 33 በመቶው ባለፉት ሶስት ዓመታት መመዝገቡን ጠቅሰው፤ በካዳስተር ስርዓት መሬትን የማስተዳደር ስራ በስፋት እየተሰራ ነው ብለዋል። ለአብነትም የአዳማ ከተማን ጨምሮ ሌሎች ከተሞች የመሬት ምዝገባ ማጠናቀቃቸው አብራርተዋል። የከተሞችን ሃብትና ገቢ የማመንጨት አቅም ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራትም ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ እንደሚገኙ አብራርተዋል። በዚህም አሁን ላይ የከተሞች ገቢ ከአራት ዓመታት በፊት ከነበረበት 10 ቢሊዮን ብር ወደ 80 ቢሊየን ብር ማድረስ እንደተቻለ ገልጸዋል። ይህም የከተሞችን ገቢ የመሰብሰብ አቅም በማሳደግ በሚያመነጩት ገቢ መጠን በመጠቀም ብድር የሚያገኙበት ሥርዓት እየተዘረጋ መሆኑን ተናግረዋል።