ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የጅማ ዞን አርሶ አደሮች ቡናን በጥራት ለገበያ በማቅረባቸው ተጠቃሚ ሆነዋል
Jul 15, 2026 44
ጅማ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ ቡናን በጥራት ለገበያ በማቅረባቸው ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን የጅማ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። አርሶ አደሮቹ ከልማዳዊ አሰራር በመላቀቅ ቡናን በባለሙያ ታግዘው በማልማትና በማዘጋጀት ለገበያ እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የጅማ ዞን ጮራ ቦቶር ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሁሴን ቶላ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በግብርና ምርምር ማዕከልና በግብርና ጽሕፈት ቤት ባለሙያዎች ታግዘው የቡና ጥራትን ለማሻሻል ሲሰሩ ቆይተዋል።   በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጥና በሽታን የሚቋቋም የቡና ዝርያን ማልማታቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም ቡናን ከምርት ጀምሮ ለገበያ እስከሚቀርብበት ጊዜ ድረስ ለጥራት ትኩረት መስጠታቸውን ተናግረዋል። በዚህ ዓመት እስካሁን 5ሺህ ኪሎግራም ጥራቱን የጠበቀ ደረቅ ቡና አዘጋጅተው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። አሁን ላይ የገበያ ትስስር ችግር እንደሌለና በመንግስት በኩል ለዘርፉ ትልቅ ትኩረት መሰጠቱ ተነሳሽነታቸው እያደገ መሆኑን አስታውቀዋል። ከአራት ዓመታት በፊት በግብርና ጽሕፈት ቤት ድጋፍ የተሻሻለ የቡና ዝርያ ቀርቦላቸው ማልማታቸውን የተናገሩት ደግሞ አርሶ አደር ታጁ ያደታ ናቸው።   ቡናን ከአመራረት ጀምሮ በዝግጅትና ለገበያ እስከማቅረብ ሂደት ጥራቱን የጠበቀ እንዲሆን የባለሙያ ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው መሆኑን ተናግረዋል። ዘንድሮ የቡና ምርታቸውን በጥራት በመሰብሰብና በማዘጋጀት ለገበያ ማቅረባቸውን ጠቅሰዋል። በዘርፉም ከራሳቸው አልፈው ለሌሎችም የስራ ዕድል መፍጠራቸውን አስታውቀዋል። የጅማ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሚፍታህ ጋሊ፣ ዞኑ በቡና ምርት የሚታወቅ እንደመሆኑ ለምርቱ ጥራት ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል ።   በተለይም ከጥቂት ዓመታት ወዲህ የገበያ ትስስርን በማስፋት፣ ለአምራቹ በቂ ግንዛቤና ስልጠና በመስጠት እንዲሁም ክትትል በማድረግ ትልቅ ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል ብለዋል። በተጠናቀቀው በጀት አመት ጥራቱን ጠብቆ የተዘጋጀ 102 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን ጠቁመው ለገበያ ከቀረበው ቡና ውስጥ 41 ሺህ ቶኑ የታጠበና ቀሪው ደረቅ መሆኑን ተናግረዋል። የቡና ልማትን ለማስፋፋትና ጥራቱን የበለጠ ለማሳደግ የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን በማዘጋጀት ለአርሶ አደሩ የማድረስ ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን አመልክተዋል። ዘንድሮም 700 ሚሊዮን የቡና ችግኞችን በማሰራጨት ተከላው እየተካሄደ መሆኑን አስታውቀዋል።
በዞኖቹ የተተገበሩ አዳዲስ የግብርና ልማት ኢኒሼቲቮች የአርሶ አደሮችን ሕይወት በተጨባጭ እየቀየሩ ነው
Jul 15, 2026 76
አዳማ ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በኢሉ አባቦር እና ባሌ ዞኖች የተተገበሩ አዳዲስ የግብርና ልማት ኢኒሼቲቮች የወጣቶችንና የአርሶ አደሮችን ሕይወት በተጨባጭ እየቀየሩ መሆኑን የዞኖቹ አስተዳዳሪዎች ገለጹ። በአዳማ አባ ገዳ አዳራሽ እየተካሄደ በሚገኘው የክልል መንግሥት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ላይ የተሳተፉ የዞን አስተዳዳሪዎች እንደተናገሩት ኢኒሼቲቮቹ በሁሉም መልኩ ስኬታማ እየሆኑ ነው። የኢሉ አባቦር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ፤ ዞኑ ያለውን የተፈጥሮ ሀብት ወደ ዕድል በመቀየር በሁሉም ረገድ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች ለውጥ እያመጡ ነው ብለዋል። ዞኑ በተፈጥሮ ደን የበለጸገ መሆኑንና ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ በተሰጠው ትኩረት በተከናወነው ሥራ የደን ሽፋኑ መጨመሩን ገልጸዋል። ይህንን ያለውን አቅም ወደ ዕድል በመቀየር ረገድ በተከናወነው ሥራ የማር ልማት ኢኒሼቲቭ በሰፊው የተሰራበት መሆኑን ጠቅሰው ይህም በተለይ ወጣቶችን እና አርሶ አደሮችን የበለጠ ተጠቃሚ ማድረጉን ተናግረዋል።   በዚህም በየዓመቱ ዘመናዊ የንብ ማነቢያ ቀፎዎችን በማሰራጨት በዞኑ የማር ልማት በከፍተኛ ደረጃ እንዲስፋፋ መደረጉን አቶ እንዳልካቸው ገልጸዋል። በማር ልማት ሥራ ላይ የተሰማሩ ወጣቶችና አርሶ አደሮችም የማር ምርታቸውን እስከ ውጭ አገር ገበያ ድረስ በማቅረብ ሕይወታቸውን እየቀየሩ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዞኑ የሻይ ቅጠል ልማት ኢኒሼቲቭ ባለፉት ጥቂት ዓመታት አመቺ ሁኔታ ባላቸው ወረዳዎች ውስጥ እንዲስፋፋ በመደረጉ ኢኒሼቲቩ ለብዙዎች የሀብት ምንጭ እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል። በባሌ ዞንም የግብርና ሥራን በሜካናይዜሽን በመደገፍ ምርታማነትን ለመጨመር የተከናወኑ አዳዲስ ኢኒሼቲቮች ውጤት ማምጣታቸውን የዞኑ አስተዳዳሪ ገልጸዋል። በዚህም በዞኑ የግብርና ሥራን በሜካናይዜሽን በመደገፍ ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር እየተከናወነ ባለው ሥራ ተጨባጭ ውጤት እየተገኘ መሆኑን የዞኑ አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሀኪም አሊይ ገልጸዋል።   በአሁኑ ወቅት በዞኑ ከ72 በመቶ በላይ የሚሆነው የግብርና ሥራ በሜካናይዜሽን እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው በዓመት ከ800 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ተግባር ቀጥሏል ብለዋል። በዞኑ በዓመት በክረምት፣ በበልግ ዝናብ እና በበጋ መስኖ ምርት እየተመረተ ሲሆን ይህም የአርሶ አደሩን የኑሮ ዘይቤ ከመቀየር ባለፈ ተጠቃሚነትን እያሳደገ መሆኑን ገልጸዋል። በተመሳሳይ በክልሉ ከተሞች የተተገበረውን የግብርና ኢኒሼቲቭ በመጠቀም የነዋሪውን ሕይወት ማሻሻል መቻሉን የተናገሩት ደግሞ የሞጆ ከተማ ከንቲባ አቶ ጋዛሊ ሀሹ ናቸው። የከተማ ግብርና ኢኒሼቲቭ በተቀናጀ መንገድ ሥራ ላይ እየዋለ መሆኑን የገለጹት አቶ ጋዛሊ፤ የከተማዋ ነዋሪዎች የራሳቸውን ፍላጎት ከመሙላት አልፈው ምርታቸውን ለገበያ በማቅረብ ሕይወታቸውንና ኑሯቸውን እየቀየሩ መሆኑን አስረድተዋል። የከተማ ግብርና በግለሰቦችና በተለያዩ ተቋማት ባዶ ቦታዎች ላይ በዘመናዊ መንገድ የተለያዩ ምርቶች እንዲመረቱ በማድረግ የምርት አቅርቦት እጥረትን እየቀረፈ መሆኑንም አንስተዋል። ይህ የከተማ ግብርና ኢኒሼቲቭ ያሉትን ዕድሎች ሁሉ በመጠቀም እንዲለማ መደረጉ የከተማዋን ነዋሪ የሥራ ባህል ከመሠረቱ እየቀየረው መሆኑንና በርካታ ሥራ ፈላጊ ወጣቶችም ተደራጅተው በከተማ ግብርና ላይ በመሰማራት ኑሯቸውን ከመሠረቱ እየቀየሩ መሆኑን ገልጸዋል።
የከተማዋን የገቢ አቅም በማሳደግ የህብረተሰቡን ጥያቄ ለመመለስ እየተሰራ ነው
Jul 14, 2026 556
ሰመራ፤ ሐምሌ 7/2018(ኢዜአ)፦ የገቢ አቅምን በማሳደግ ህብረተሰቡ ለሚያነሳቸው የልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር አህመድኑር ሳሊም ገለጹ ። የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ ጋር በመተባበር የገቢና የአስተዳደር ብቃት አቅምን ለማሳደግ የሚያስችል የስልጠናና የልምድ ልውውጥ መድረክ እያካሄደ ነው።   የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር አህመድኑር ሳሊም በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የገቢ አቅምን በማሳደግ ማሕበረሰቡ የሚያነሳቸውን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ለሚያስችሉ ተግባራት ትኩረት ተሰጥቷል። በተለይ ለህብረተሰቡ የሚሰጡ አገልግሎቶችን በማሻሻል የከተማዋን የመሠረተ ልማት ፍላጎት ለማሟላት የሚያስችሉ ስልቶች ተነድፈው ተግባራዊ መደረጋቸውን ነው የገለጹት። በዛሬው እለት የተጀመረው ስልጠና እና የልምድ ልውውጥም ከተማዋ የገቢና ወጪ ኮሪደር ከመሆኑዋ ጋር ተያይዞ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አገልግሎቱን የተመቸ ከማድረግ አንፃር ልምድ የሚቀመርበት መሆኑን ገልፀዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ የትምህርትና ስልጠና ዳይሬክተር ወይዘሮ አስቴር ተሰማ በበኩላቸው ፤በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የገቢ አቅምን አሟጦ በመጠቀም የህብረተሰብ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ተችሏል።   ከስድስት የተመረጡ የአፍሪካ ከተሞች በፕሮጀክት አፈፃፀም አንደኛ በመሆን እንደተመረጠች እና አስተዳደሩ ይሕንን ልምድ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚያስፈልገው ነው የተናገሩት። ከተማ አስተዳደሩ የገቢ አቅሙን በማሳደግ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ አገልግሎት መስጫ ተቋማትን በስፋት ለማልማት እንደቻለም አመልክተዋል። የገቢ አቅም ማሳደግ በሚፈለገው መልኩ መሠረተ ልማቶችን ለመገንባት እና ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል በመሆኑም ይሕንንም እንደ ልምድ ወስዶ መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል። በስልጠናውና በልምድ ልውውጡ በታክሰ መረጃ አሰባሰብ፣ በኦዲት ፣ በገቢ ግብር አዋጅ ፣በተጨማሪ እሴት ታክስ አዋጅና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ያሉ መመሪያዎች እና አሰራሮች በዝርዝር እንደሚዳሰሱም ነው የገለጹት። ለሶስት ቀናት በሚቆየው የልምድ ልውውጥና ስልጠና ላይም የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፊዎችና ከፍተኛ ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ ናቸው።
የደብረ ማርቆስ አውሮፕላን ማረፊያ ለጥያቄዎቻችን ምላሽ የሰጠ ነው- ነዋሪዎች
Jul 14, 2026 376
ደብረ ማርቆስ ፤ ሐምሌ 7/2018(ኢዜአ)፦ የደብረ ማርቆስ ንጉስ ተክለ ሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያ መገንባት ለመሰረተ ልማት ጥያቄዎቻችን ምላሽ የሰጠና ለአካባቢው ሁለንተናዊ እድገት ብሩህ ተስፋ የሰነቀ ነው ሲሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የደብረ ማርቆስ ንጉስ ተክለ ሃይማኖት አውሮፕላን ማረፊያን ከቀናት በፊት መርቀው አገልግሎት አስጀምረዋል። በዚሁ ሁነት ላይ ባስተላለፉት መልእክትም የአውሮፕላን ማረፊያው ተመርቆ ለአገልግሎት መብቃቱ የደብረ ማርቆስ ከተማና አካባቢውን ነዋሪዎች የዘመናት ጥያቄ የመለሰ መሆኑን ገልጸዋል።   ለ30 ዓመታት ተቋርጦ የቆየው ኤርፖርት ግንባታው ተጠናቆ ስራ መጀመሩ የአካባቢውን የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ በማነቃቃት ለኢኮኖሚ ዕድገት አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ይሆናል ብለዋል። አስተያየታቸውን የሰጡ የደብረ ማርቆስ ከተማ ነዋሪዎች፤ የአውሮፕላን ማረፊያው መገንባት ለልማት ጥያቄዎቻችን ምላሽ የሰጠና ለአካባቢው ሁለንተናዊ እድገት ብሩህ ተስፋ የሰነቀ ነው ሲሉ ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ የቆየ ዓለሙ፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ስራ መጀመር የለውጡ መንግስት የነዋሪውን ለዘመናት የቆየ የመሰረተ ልማት ጥያቄ ምላሽ የሰጠ በመሆኑ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶናል ብለዋል። የኔፋንታ ተገኝ እና ጥላሁን ፋንታሁን የተባሉ ነዋሪዎችም ፤ የአውሮፕላን ማረፊያ መገንባቱ የደብረማርቆስ ከተማና አካባቢው ሕዝብ ለረጅም አመታት ሲያቀርበው ለነበረው የመሰረተ ልማት ጥያቄ ምላሽ የሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ለሕክምና ፣ ለንግድና ለሌሎች አስቸኳይ ጉዳዮች ወደ አዲስ አበባ የሚደረጉ ፈጣን ጉዞዎችን ለማድረግ ሁነኛ መፍትሄ በመሆኑ ተደስተናል ብለዋል። ወይዘሮ እኔምአየሁ ጌቴ እና አቶ ነብዩ ብርሃኑ፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታ ተጠናቆ አገልግሎት መጀመሩ ለከተማዋና አካባቢው ህዝብ ትልቅ ስኬትና ደስታ መሆኑን ተናግረዋል። የለውጡ መንግስት የህዝብን ጥያቄ በማድመጥ ለአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታ ትኩረት በመስጠት ለስኬት በማብቃቱ የላቀ ምስጋና ይገባዋል ብለዋል።
በዞኑ የተገነቡ አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ግድቦች የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ አደጋ የመቋቋም አቅም አሳድገዋል
Jul 14, 2026 331
አዳማ፤ ሐምሌ 7/2018(ኢዜአ)፦ በቦረና ዞን የተገነቡ አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ግድቦች የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ አደጋ የመቋቋም አቅም መሳደጋቸውን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አብዱሰላም ዋሪዮ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሰሞኑን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ልማትን በማስመልከት በሰጡት ማብራሪያ ቀደም ሲል በድርቅ ይፈተን የነበረው የቦረና አካባቢ በአሁኑ ወቅት በስንዴ ልማት ትልቅ ስራ እየሰራ መሆኑን አንስተዋል።   የኦሮሚያ ክልል መንግስትም የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ኑሮ ለማሻሻልና የእንስሳት ሀብቱን ከአደጋ ለመጠበቅ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። ከዚህ ውስጥ የአርሶና አርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስና የኑሮ ሁኔታን ለማሻሻል መለስተኛ እና አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ ዋነኛው ነው። የክልሉ መንግስት 'ፊና' ብሎ በሰየመው የአነስተኛ እና መለስተኛ ግድቦች ግንባታ ፕሮጀክት ተጠቃሚ ከሆኑት ዞኖች መካከል የቦረና ዞን አንዱ ነው።   የቦረና ዞን ዋና አስተዳዳሪ አብዱሰላም ዋሪዮ፤ በዞኑ የአርብቶ አደሩን ድርቅ የመቋቋም አቅም ለማሳደግ እየተከናወኑ ባሉ ሥራዎች ውጤቶች እየተመዘገቡ ነው ብለዋል። የቦረና ዞን ለዝናብ እጥረት እና ድርቅ የተጋለጠ መሆኑን አንስተው፣ የ'ፊና' ፕሮጀክት ተግባራዊ መሆን ከጀመረ ወዲህ ግን ይህ ችግር እየተፈታ መምጣቱን ገልጸዋል። እስካሁን አገልግሎት መስጠት የጀመሩ የመስኖ ግድቦች የዝናብ ውሃን በመያዝ የዝናብ እጥረት በሚከሰትበት ጊዜ ጥቅም ላይ እንዲውል እየተደረገ የማህበረሰቡ የድርቅ አደጋን የመቋቋም አቅም እየተገነባ መሆኑን ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅት በቦረና ዞን 18 የፊና ፕሮጀክቶች ውሃ በመያዝ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ አስታውሰው በዚህም የአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ የእንስሳት መኖ፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ ስንዴ እና የተለያዩ የሰብል ዓይነቶችን እያመረተ ይገኛል ብለዋል። በተጨማሪም የመስኖ ግድቦቹን በመጠቀም የእንስሳት መኖ በማልማት፣ ድርቅ በሚከሰትበት ጊዜ እንስሳት ለችግር እንዳይጋለጡ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ነው ያሉት። እነዚህ ፕሮጀክቶች የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ አደጋን የመቋቋም አቅም ከማሳደግ ባለፈ፣ የሥራ ባህልን እየቀየሩ መሆኑንም አስረድተዋል። የኦሮሚያ ክልል መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ መረጃ እንደሚያመለክተው በ'ፊና' ፕሮጀክት ስር 37 የመስኖ ግድቦች ተጠናቀው ለአገልግሎት በቅተዋል። በዚህ ዓመትም በመስኖ ግድቦቹ 864 ሚሊየን ኪዩቢክ ሜትር ውሃ መያዝ በመቻሉ ሰፊ መሬት በመስኖ ማልማት መቻሉ ተመልክቷል።
መንግሥት የሎጂስቲክስ ዘርፉን በማዘመን የገቢና የወጪ ንግድን ቀልጣፋ በማድረግ የኢንቨስትመንት ፍሰትን ለማሳደግ በትኩረት እየሰራ ነው
Jul 14, 2026 351
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 7/2018 (ኢዜአ)፦ መንግሥት የኢትዮጵያን የሎጂስቲክስ ዘርፍ በማዘመን የገቢና የወጪ ንግድን ቀልጣፋ በማድረግ የኢንቨስትመንት ፍሰትን ለማሳደግ በትኩረት እየሰራ መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ዴንጌ ቦሩ ገለጹ። የኢትዮጵያ የዕቃ አስተላላፊዎች እና የመርከብ ወኪሎች ማኅበር (EFFSAA)፣ ከተለያዩ የመንግሥት፣ የግል እና ዓለም አቀፍ ተቋማት የተውጣጡ የሎጂስቲክስ ባለሙያዎችን በዓለም አቀፍ ዕውቅና ባለው የፊያታ (FIATA) ዲፕሎማ አሰልጥኖ አስመርቋል፡፡   በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የተገኙት የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ዴንጌ ቦሩ እንደገለጹት፤ መንግሥት ለዘርፉ ሪፎርም ልዩ ትኩረት በመስጠት ስትራቴጂ ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። ሎጂስቲክስ ዕቃዎችን ማጓጓዝ ብቻ ሳይሆን የሀገር ኢኮኖሚ ከዓለም አቀፍ ገበያ ጋር የሚያገናኝ መረብ ነው ብለዋል። መንግሥት የወጪና የገቢ ምርቶችን በሚፈለገው ፍጥነትና ጥራት ለማሳለጥ የሎጂስቲክስ ዘርፉን በሰለጠነ የሰው ኃይል ለማጠናከርና ለማዘመን ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል። በኢንዱስትሪ፣ በማዕድን፣ በቱሪዝምና በዲጂታል ኢኮኖሚ የተጀመሩ የብልጽግና ጉዞዎች ውጤታማ መሆን የሚችሉት አስተማማኝ የሎጂስቲክስ ሥርዓት ሲኖር ብቻ መሆኑን ጠቁመዋል። የሎጂስቲክስ ዘርፍ ካልዘመነ በስተቀር ምርቶችን በጥራት፣ በሰዓቱና በቅናሽ ዋጋ ለገበያ ማቅረብ እንደማይቻልና የሀገር ውስጥ ምርቶችም በዓለም መድረክ ተወዳዳሪ መሆን እንደማይችሉ አስረድተዋል።   ዛሬ የተመረቁት የፊያታ ዲፕሎማ ባለሙያዎች የሀገሪቱን የአቅርቦት ሰንሰለት በማዘመን ረገድ ትልቅ አደራና ኃላፊነት እንዳለባቸው አሳስበዋል። ሰልጣኞችና የዘርፉ ተዋናዮች ዓለም አቀፍ ኩባንያዎችና ባለሀብቶች ወደ ሀገር ውስጥ በሚመጡበት ወቅት የሚፈጠሩትን ዕድሎች ለመጠቀም ከአሁኑ ዝግጁ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፍራኦል ጣፋ በበኩላቸው፤ በሀገሪቱ የሎጂስቲክስ ሥርዓትን ማዘመንና ወቅቱን የዋጀ አሠራር መዘርጋት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል።   ለዚህም ይረዳ ዘንድ አጠቃላይ የዘርፉን ትራንስፎርሜሽን ለማሳለጥ የሚያስችል የአሥር ዓመት ስትራቴጂ ተቀርጾ ወደ ተግባር መግባቱን ይፋ አድርገዋል። በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ ያሉ ተግዳሮቶችና የኢትዮጵያ ጂኦ-ፖለቲካዊ አቀማመጥ የሚፈጥሩትን ተጽዕኖ ለመቋቋም የራስን ሥርዓት በራስ አቅም መገንባት ወሳኝ ነው ብለዋል። የውጭ ኢንቨስትመንት ዕድልን በአግባቡ ለመጠቀምና የሀገሪቱን የንግድ ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ በሳይንሳዊና በዘመናዊ ዕውቀት የሰለጠኑ ባለሙያዎች ሚና የማይተካ መሆኑን አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ የዕቃ አስተላላፊዎች እና የመርከብ ወኪሎች ማኅበር ፕሬዝዳንት ዳዊት ውብሸት (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ይህ የፊያታ ዓለም አቀፍ ሥልጠና በኢትዮጵያ ያለውን የሠለጠነ የሰው ኃይል እጥረት ለመቅረፍ ትልቅ እምርታ መሆኑን ገልጸዋል።   ማኅበሩ አቅምን በመገንባትና የገበያ ትስስርን በመፍጠር ረገድ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በቅርበት እየሠራ እንደሚገኝም አብራርተዋል። ሰልጣኞች በበኩላቸው፤ የወሰዱት ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ስልጠና የሙያ ብቃታቸውን ከማሳደግ ባለፈ ሀገራቸውን በላቀ ደረጃ ለማገልገል ትልቅ መነሳሳትን እንደፈጠረላቸው ገልጸዋል።   ከኢትዮጵያ የባህር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ በስልጠናው የተሳተፉት አቶ አምባዬ ገብርኤል፤ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ስልጠና መውሰዳቸው የስራ ብቃታቸውን ለማሳደግ ከፍተኛ እገዛ አለው ብለዋል። የተሻለ ሥራ ለመሥራትና ሀገራቸውን በላቀ ሁኔታ ለማገልገል ቁርጠኛ መሆናቸውን ተናግረዋል።   ከፔቭ ሎጂስቲክስ የመጡትና የስልጠናው ተሳታፊ የሆኑት አቶ ይርጋለም አዲስ በበኩላቸው፣ ስልጠናው ትልቅ እውቀትና ክህሎት እንዳስጨበጣቸው ገልጸዋል።
በክልሉ በበጀት ዓመቱ 47 አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ወደሥራ ገብተዋል
Jul 14, 2026 185
ሐረር፤ ሐምሌ 7/2018 (ኢዜአ)፡-በሐረሪ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 47 አዳዲስ አነስተኛ እና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ወደ ማምረት ሥራ የገቡ ፋበሪካዎች ለዜጎች የሥራ ዕድል እየፈጠሩ መሆኑም ተመላክቷል። የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ሃላፊ ኡስማኢል ዩስፍ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ለማስፋፋት ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።   በተለይም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪውን የማምረት አቅም ከማሳደግ ባለፈ በዘርፉ ትልቅ መነቃቃት እየፈጠረ ይገኛል ብለዋል። በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት ሰባት መካከለኛ እና 47 አነስተኛ አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ወደሥራ እንደገቡ ገልጸው፣ ተጨማሪ 16 አዳዲስ ኢንዲስትሪዎች ደግሞ የግንባታ ሥራቸውን አጠናቀው ወደማሽነሪ ተከላ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። እንደ ቢሮ ሀላፊው ገለጻ በክልሉ ወደሥራ የገቡት ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጪ ምንዛሬን ከማስቀረት አንጻር ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ። አምራች ኢንዱስትሪዎቹ ከሃይል አቅርቦት፣ ከመሰረተ ልማት ጋር በተያያዘ ያሉባቸውን ችግሮች ለመፍታት መሰራቱን ገልጸው፣ ዘንድሮ በኢንዱስትሪ ዘርፉ ብቻ 621 ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የሥራ እድል ተፈጥሯል ብለዋል።   በመንግስት የተፈጠረላቸውን ምቹ ሁኔታ ተጠቅመው በተደራጁበት የፈርኒቸር ሥራ ዘንድሮ ወደ ማምረት መሸጋገራቸውን የገለጸው ደግሞ ወጣት መሃዲ አብዱልዋሲ ነው። ወደፊት ምርታቸውን በጥራት በማምረት ወደ ውጭ የመላክ እቅድ መያዛቸውን ጠቁሞ፣ ከማህበሩ አባላት በተጨማሪ ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም ተናግሯል። የስንዴ ዱቄት በማምረት ለአካባቢው እያከፋፈሉ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ በሐረር ከተማ ኢንዱስትሪ ዞን የሚገኘው የቀነኒ ፉድ ኮምፕሌክስ ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ አቶ ተስፋ አስፋው ናቸው።   በአሁኑ ወቅትም ዘመኑን የዋጀ የማምረቻ ማሽን በከፍተኛ ወጪ ከውጭ አገር በማስመጣት የማስፋፊያ ሥራ እያከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። የክልሉ መንግስት ለአምራች ኢንዱስትሪዎች የፈጠረው ምቹ ሁኔታ ስራቸውን ይበልጥ ተግተው እንዲሰሩ የሚያበረታታ መሆኑንም አክለዋል። በፋብሪካው የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው መካከል ቢሻው ሃይሉ እንደተናገረው፣ በክልሉ የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት የሥራ ዕድል ተጠቃሚነትን ከማጎልበት ባሻገር አዳዲስ የቴክኖሎጂ እውቀቶችን ለማሽጋገር እያገዘ ነው።      
በምስራቅ ቦረና ዞን የገቢ አሰባሰብን ዲጂታላይዝድ በማድረግ ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ ተችሏል
Jul 14, 2026 136
ነገሌ፤ ሐምሌ 7/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ቦረና ዞን የገቢ አሰባሰብ ሒደቱን ዲጂታላይዝድ በማድረግ በበጀት ዓመቱ ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉን የዞኑ ገቢዎች ጽሕፈት ቤት ገለጸ፡፡ በጽሕፈት ቤቱ የዕቅድ፣ በጀት ክትትልና ግምገማ ባለሙያ መዓዛ አሊ እንዳሉት በዞኑ የገቢ አሰባሰብ ሒደት ቀልጣፋና ፍትሐዊ ለማድረግ የዲጂታል አሠራር ተዘርግቷል። በዚህም በበጀት ዓመቱ ከተለያዩ የገቢ ርዕሶች ለመሰብሰብ ከታቀደው ከ1 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ውስጥ ከ1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ከዞኑ የተሰበሰበው ዓመታዊ ገቢ ከዕቅዱ በ311 ሚሊዮን 917 ሺህ ብር ብልጫ እንዳለው አስታውቀዋል፡፡ የገቢ አሰባሰቡን ውጤታማ ለማድረግም የዲጂታል ቴክኖሎጂ አሠራር መዘርጋቱና ግብር መክፈል የዜግነት ግዴታ መሆኑን ተከታታይ የግንዛቤ መድረክ መፈጠሩን አንስተዋል። ግብራቸውን በታማኝነትና በወቅቱ በመክፈል የዜግነት ድርሻቸውን መወጣታቸውን ያስረዱት ደግሞ በነገሌ ቦረና ከተማ የሕንጻ መሣሪያ አቅራቢና አከፋፋይ አቶ ወርቁ ኦዳ ናቸው። የሚከፍሉት የሥራ ግብር ለመሠረተ ልማት ግንባታ በመዋል ተመልሶ ሕዝብን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን በመገንዘባቸው ግብርን በጊዜ መክፈላቸውን አክለዋል።   በከተማው በሸቀጣሸቀጥ ንግድ ሥራ የተሰማሩት አቶ ቢኒያም አሰፋ በበኩላቸው ግብርን መክፈል የዜግነት ግዴታ እና ለአገር ልማት ነው ብለዋል፡፡ በታማኝነት ግብር መክፈል ዘላቂ ሰላምና ልማት ለማረጋገጥ ወሳኝ በመሆኑ ሁሉም ኃላፊነቱን እንዲወጣም አስተያየታቸውን አጋርተዋል።   የሚከፍሉት ግብር ለአገር ልማት የራሱ ድርሻ እንዳለው የጠቆሙት ደግሞ በንግድ ሥራ የተሰማሩት አቶ ሰይድ በድሩ ፤በታማኝነት ግብራቸውን በመክፈል ፍትሐዊ የንግድ ውድድር እንዲሰፍንና የሕዝቡ የመሠረተ ልማት ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ የበኩላቸውን መወጣታቸውን ጠቁመዋል፡፡  
ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ሁለት የብድር ስምምነት ረቂቅ አዋጆችን መርምሮ አጸደቀ
Jul 14, 2026 313
አዲስ አበባ፣ሐምሌ 7/2018 (ኢዜአ):-ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ሁለት የብድር ስምምነት ረቂቅ አዋጆችን መርምሮ አጸደቀ። ስድስተኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 2ኛ አስቸኳይ ስብሰባውን አካሂዷል።   ምክር ቤቱ በዛሬው ስብሰባው በኢትዮጵያ እና በጣሊያን ሪፐብሊክ መንግሥት፣ እንዲሁም ከዓለም ባንክ ለሦስተኛው የኢትዮጵያ ዕድገትና ልማት ፖሊሲ ክንውን ጋር በተጣጣመ መልኩ ለዘላቂ እና አስተማማኝ ልማት ለኢትዮጵያ የሚሰጥ የበጀት ድጋፍ ማስፈጸሚያ የሚውል የብድር ስምምነትን በሙሉ ድምፅ አጽድቋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ ቤልጂጌ (ዶ/ር) የብድር ስምምነቱን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፣ የብድር ስምምነቱ 70 ሚሊዮን ዩሮ ሲሆን ምንም ዓይነት የአገልግሎት ክፍያ እንደማይጠየቅበት ገልጸዋል። ብድሩ ቀጥታ ወደ መንግሥት በጀት ፈሰስ የሚደረግ መሆኑን ጠቁመው፣ የማክሮ ኢኮኖሚ ትግበራውን በማሳለጥ ዕድገትን ለማፋጠን አጋዥ ነው ብለዋል። የብድር ስምምነቱ 16 ዓመት የችሮታ ጊዜ ያለው ሲሆን፣ በ30 ዓመት ጊዜ ውስጥ ተከፍሎ የሚጠናቀቅ የረጅም ጊዜ ብድር መሆኑን ተናግረዋል። ምክር ቤቱ የብድር ስምምነቱን ረቂቅ አዋጅ በሙሉ ድምፅ አጽድቋል።   በተመሳሳይ ምክር ቤቱ በኢትዮጵያ መንግሥት እና በፈረንሳይ መንግሥት መካከል የትዕዛዝ ቁጥጥርና ንብረት አስተዳደር ሥርዓቶችን የደረጃ አወጣጥ የዲጂታላይዜሽን ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውል የብድር ስምምነትን መርምሮ በሙሉ ድምፅ አጽድቋል። በምክር ቤቱ የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ስምምነቱን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፣ ስምምነቱ 54 ሚሊዮን 600 ሺህ ዩሮ የፋይናንስ ድጋፍ ስምምነትን የያዘ መሆኑን ተናግረዋል። የብድር ስምምነቱ በ10 ዓመት የችሮታ ጊዜ ውስጥ በ25 ዓመት ተከፍሎ የሚጠናቀቅ መሆኑን ጠቅሰው የወለድ መጠኑም 0 ነጥብ 347 በመቶ ዝቅተኛ መጠን ያለው መሆኑን አብራርተዋል። የብድር ስምምነቱ የኢትዮጵያን ዲጂታላይዜሽን ጉዞ የሚያፋጥን እንደሆነም ጠቅሰዋል።
በክልሉ የአርሶና አርብቶ አደሩን ኑሮ በዘላቂነት ማሻሻል የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jul 14, 2026 218
አዲስ አበባ፣ሐምሌ 7/2018 (ኢዜአ):-በኦሮሚያ ክልል በግብርናው ዘርፍ የአርሶና አርብቶ አደሩን ኑሮ በዘላቂነት ለማሻሻል የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኝ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ በ2018 የበልግ አዝመራ ከ500 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የደረሰ ሰብል መሰብሰቡም ተገልጿል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ በሪሶ ፈይሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በግብርናው ዘርፍ የአርሶና አርብቶ አደሩን ኑሮ በዘላቂነት ለማሻሻል የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በዚሁ መሰረት ባለፉት ዓመታት አርሶና አርብቶ አደሩ በሁሉም የአርሻ ወቅቶች በግብርና ልማት ሥራ ላይ እንዲሰማራ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። በተያዘው የምርት ዘመን በበልግ ወቅት በተለይም በቆላማ አካባቢዎች የሚኖሩ አርሶና አርብቶ አደሮች በግብርና ሥራ ላይ በስፋት በመሳተፍ፣ በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ገበያውን ለማረጋጋት የሚያግዙ ተግባራትን ማከናወናቸውን ገልጸዋል። በክልሉ በ2018 በልግ አብቃይ በሆኑ ዞኖች ወደ 2 ሚሊዮን ሄክታር የሚጠጋ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መልማቱን አመልክተዋል። ለአርሶ አደሩ ድርቅን መቋቋም የሚችሉና በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚደርሱ የስንዴ፣ ማሽላ፣ በቆሎ፣ ቦሎቄ እና ዳጉሳ ያሉ የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎች እንዲቀርቡ መደረጉንም ጠቁመዋል። በክልሉ የበልግ እርሻ በስፋት ከሚከናወንባቸው አካባቢዎች መካከል ባሌ፣ ምስራቅ ባሌ፣ ጉጂ፣ ምዕራብ ጉጂ፣ ምስራቅ ሐረርጌ፣ ምዕራብ ሐረርጌ፣ አርሲ፣ ምዕራብ አርሲ እና ቦረና ዞኖች በዋናነት ተጠቃሽ እንደሆኑም አቶ በሪሶ አንስተዋል። በአሁኑ ወቅት በበልግ የለማው ሰብል ደርሶ መሰብሰብ መጀመሩን የገለጹት ምክትል ኃላፊው፣ እስካሁን በ500 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የለማው ሰብል መሰብሰቡን አረጋግጠዋል። ለበልግ አዝመራው ስኬታማነት የክልሉ ግብርና ቢሮ የአፈር ማዳበሪያና የተለያዩ የተሻሻሉ ምርጥ ዘሮችን በወቅቱ ለአርሶና አርብቶ አደሩ ማቅረቡን ገልጸው፤ ከመሬት ዝግጅት ጀምሮ እስከ ሰብል አሰባሰብ ድረስም ያልተቋረጠ ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል። ከትናንት ጀምሮ እየተካሄደ ባለው የክልሉ መንግስት የበጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ላይ ክልሉ የግብርናውን ዘርፍ ምርታማነት ለማሳደግ የተተገበሩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችና የተደረጉ ሁለንተናዊ ድጋፎች በዘርፉ ከፍተኛ ውጤት ማስገኘታቸው ተመልክቷል። ለዚህም ማሳያ የሚሆነው በከተሞችና በገጠር አካባቢዎች የወተት ላሞች እርባታ በዘመናዊ መንገድ መተግበሩና ምርጥ የእርባታ ዶሮዎች ለአርሶ አደሩ መሰራጨታቸው መሆኑ ተመላክቷል። በዓሣ እርባታም የዓሣ ጫጩቶች ለአርሶ አደሩና ለአርብቶ አደሩ ተሰራጭተው ወደ እርባታ ኩሬዎች መግባታቸውን ነው የተገለጸው።  
በጀቱ በከተማ አስተዳደሩ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር የሚያስችል ነው
Jul 13, 2026 624
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት ለ2019 በጀት አመትያጸደቀው በጀት በከተማዋ የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር የሚያስችል መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ የፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱልቃድር ሬድዋን ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ጉባኤው የከተማ አስተዳደሩን ለ2019 በጀት ዓመት 502 ነጥብ 27 ቢሊዮን ብር በጀት አፅድቋል። የከተማ አስተዳደሩ የፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ አብዱልቃድር ሬድዋን ለ2019 በጀት ዓመት 502 ነጥብ 27 ቢሊዮን መሆኑን ተናግረዋል። በበጀት ድልድሉ የመደበኛ በጀትን በቁጠባ ጥቅም ላይ እንዲውል ታሳቢ በማድረግ የበጀት ጭማሪው በዋናነት ለካፒታል ፕሮጀክቶች እንዲሆን መደረጉን ተናግረዋል። በዚህም መሠረት የካፒታል በጀቱን 71 ነጥብ 5 በመቶ ድርሻ ያለው ሲሆን መደበኛ ወጭ ከአጠቃላይ በጀቱ 25 ነጥብ 3 በመቶ ድርሻ እንዳለው ተናግረዋል። በጀቱ በዋናነት እድገት ተኮር በሆኑ ዘርፎች እንዲውል በማድረግ ሰፋፊ የሰው ተኮር የልማት እንቅስቃሴ ለማጠናከር ነው ብለዋል። በዓይነት እንዲሁም በመጠን ሰፋፊ የከተማ ግንባታና የመልሶ ማልማት ስራዎችን በማከናወን የከተማዋን እድገት ለማሳለጥ ነው ብለዋል። በጀቱ የከተማዋን የልማት ፍላጎትና የአገልግሎት ደረጃ ይበልጥ ለማሳደግ ታሳቢ ተደርጎ የተመደበ ሲሆን፣ የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎችን አጠናክሮ ለመቀጠል የሚያስችል እንደሆነ አመላክተዋል። በተጨማሪም ለማህበራዊ ልማት፣ ለውሃ አቅርቦትና ሁሉንም አቀፍ የልማት ሥራዎች በተሳለጠ መንገድ ለማቅረብ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። ከፍተኛ ድርሻ የያዘው የካፒታል በጀቱ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለቤት ልማት፣ ለመሠረተ ልማት ግንባታ፣ የትራንስፖርት አገልግሎትን ማሻሻልና አጠቃላይ የከተማዋን ልማትና ዕድገት ይበልጥ ለማዘመን የተመደበ እንደሆነ ገልፀዋል።        
የኢትዮጵያ የእንስሳት ሃብት ልማት የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት በማሻሻል ውጤት እያስገኘ ነው
Jul 13, 2026 325
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የእንስሳት ሃብት ልማት የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት በማሻሻል ውጤት እያስገኘ መሆኑን የግብርና ሚንስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የግብርና ሚኒስቴር ከአፍሪካ ህብረት የአህጉር-አቀፍ የእንስሳት ሃብት ቢሮ በመተባበር የተዘጋጀው ጉባኤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው።   የግብርና ሚንስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ፤ ኢትዮጵያ የእንሰሳት ሃብት ልማት በማሳደግ የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተጨባጭ እርምጃዎችን በመውሰድ እየሰራች ነው። በዚህም አርሶና አርብቶ አደሮች የሚያጋጥሟቸውን የውሃና የመኖ እጥረትን በዘላቂነት የሚቀርፉ እንዲሁም የእንስሳት ሕክምና መስጫ ተቋማትን የማስፋፋት ስራዎችን እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከአርብቶ አደሮች ጋር የሚሰሩ ተቋማትን፣ የእንስሳት ገበያ ማዕከላትን ለአርብቶ አደር አካባቢዎች ተደራሸነት የማጠናከር ስራዎችንም እየተሰራበት እንደሆነም አብራርተዋል። የአፍሪካ አርብቶ አደሮች ገበያ ልማት ላይ ያተኮረው ጉባኤ የአፍሪካ ሀገራት የግብርና-ምግብ ስርዓቶቻቸውን ለማጠናከር፣ በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ስር ያለውን የአህጉር ውስጥ ንግድ ለማስፋፋት እና የእንስሳት እና አርብቶ አደር የምርት ስርዓቶችን ሙሉ ኢኮኖሚያዊ አቅም ለመጠቀም በሚጥሩበት በዚህ ወሳኝ ወቅት ላይ የተዘጋጀ ነው ብለዋል። በአፍሪካ አገራት መካከል የእውቀት ሽግግሮችን ማጠናከር፣ ኢንቨስትመንቶችን ማስተባበር እና በመላው አፍሪካ የሚገኙ ማህበረሰቦችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ድንበር ተሻጋሪ መፍትሄዎችን ማዘጋጀት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የእንስሳት ሀብት ልማቱን ከማዘመን ፣ምርታማነትንና የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ከማሳደግ አኳያ ተጨባጭ ለውጦች መገኘታቸውንም ገልጸዋል።   በአፍሪካ ህብረት የእንስሳት ሀብት ቢሮ ዳይሬክተር ሁያም ሳሊህ ( ዶ/ር) አፍሪካ የዓለምን የእንስሳት ሃብት ከፍተኛ ድርሻ ብትይዝም፣ ከእሴቱ ግን የምታገኘው በጣም አነስተኛውን ድርሻ ነው ብለዋል። በቀጣይም የአህጉሪቷን ግዙፍ የእንስሳት ሃብት በማልማት የአርሶና አርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማሻሻል በሁሉም ዘርፍ የኢንቨስትመንት አማራጮችን ማስፋት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። በአፍሪካ ህብረት የእንስሳት ሀብት ቢሮ የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ከአጋር አካላት ጋር እየተሰሩ ያሉ ስራዎችንም አንስተዋል።   በአፍሪካ ህብረት የገጠር ልማት ክፍል ኃላፊ እና የግብርናና ምግብ ዋስትና ክፍል ተጠባባቂ ኃላፊ ጃኔት ኤደሜ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአፍሪካ የእንስሳት ልማት ኢንዱስትሪ ተወዳዳሪ ማድረግ፣ ቀጣናዊ ውህደት እንዲሁም የግል ዘርፉ ተሳትፎ ለማጠናከር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በአፍሪካ የእንስሳት ገበያ ማዕከልና ሌሎች የእንስሳት ልማት ዘርፍ ኢንቨስተመንቶችን ማሳደግና ቅድሚያ በመስጠት በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባም ነው የገለጹት። ከእንስሳት ውጤቶች ምርት ጀምሮ እስከ አገር ውስጥና የውጭ ገበያ ባለው ሂደት የእሴት ሰንሰለትን ማጠናከር የእንስሳት ጤና ጥበቃ ሥርዓትና ድንበር ተሻጋሪ የእንስሳት በሽታዎች ቁጥጥርም ማጠናከር እጅግ አስፈላጊ ነው ብለዋል።   የጌትስ ፋውንዴሽን ተወካይ ቶማስ አቤ፤ ፋውንዴሽኑ የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት፣ የገበያ ተደራሽነት ለማስፋፋት፣ የፖሊሲ እና ተቋማዊ አቅሞችን ለማጠናከር ከአፍሪካ ህብረት የእንስሳት ሀብት ክፍል ጋር እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የአፍሪካ አርብቶ አደሮችን ገበያ ልማትና ኢንቨስትመንት ለማሳደግና የፖሊሲ ማዕቀፎችን ለማጠናከር እየተሰሩ የሚገኙ ስራዎችንም ጠቅሰዋል።    
በአፋር ክልል በበጀት ዓመቱ ከ8 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰበሰበ
Jul 13, 2026 240
ሰመራ፣ ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፡-በአፋር ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ8 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ። የአፋር ክልል ገቢዎች ቢሮ ሃላፊ አቶ አወል አብዱ ዛሬ በሰጡት መግለጫ በክልሉ በበጀት ዓመቱ የክልሉን የገቢ ግብር አሰባሰብ ውጤታማ ለማድረግ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ተሰርቷል። ቅንጅታዊ ሥራውን ከማጠናከር ባለፈ አሰራርን የማዘመን ሥራ መሰራቱን ጠቅሰው፣ በእዚህም ውጤታማ የግብር አሰባሰብ ሥራ መከናወኑን አመልክተዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ 8 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደሥራመገባቱን አስታውሰው፣ በበጀት ዓመቱ ከ8 ቢሊዮን 524 ሚሊዮን ብር በላይ ተሰብስቧል ብለዋል። በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር መተግበሩ፣ የግብር ከፋዩ ማህበረሰብ ግንዛቤ እያደገ መምጣት እና በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች ቁርጠኝነት ለተገኘው ውጤት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል ብለዋል። ገቢው የተገኘው ከቀጥታ ታክስ፣ ቀጥታ ካልሆኑ ታክሶች እና ታክስ ካልሆኑ የገቢ አርዕስቶች መሆኑንም አስረድተዋል። እንደ አቶ አወል ገለጻ፣ ዘንድሮ የተገኘው ገቢ ባለፈው ዓመት ከተገኘው ገቢ ጋር ሲነጻጸር ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ ብልጫ አለው። በገቢ አሰባሰብ ላይ ቅንጅታዊ አሰራርን ከመተግበር ባለፈ ህገ-ወጥነትን ለመከላከል የተሰራው ሥራ ለውጤቱ አስተዋጾ ማድረጉንም አስታውቀዋል።  
የአዲስ አበባ ከተማ የ2019 በጀት 502 ነጥብ 27 ቢሊዮን ብር ሆኖ ጸደቀ
Jul 13, 2026 565
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ምክር ቤት ለ2019 በጀት ዓመት 502 ነጥብ 27 ቢሊዮን ብር በጀት አጸደቀ። ከበጀት ድልድሉ ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ የሚይዘው የካፒታል በጀት ሲሆን፤ 71 ነጥብ 5 በመቶ ድርሻ ያለው እንደሆነ ተገልጿል።   እንዲሁም 25 ነጥብ 3 በመቶው ለመደበኛ ወጪ ተመድቧል። በጀቱ የከተማዋን የልማት ፍላጎትና የአገልግሎት ደረጃ ይበልጥ ለማሳደግ ታሳቢ ተደርጎ የተመደበ ሲሆን፣ የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎችን አጠናክሮ ለመቀጠል የሚያስችል እንደሆነ ተመልክቷል። በተጨማሪም ለማህበራዊ ልማት፣ ለውሃ አቅርቦትና ሁሉንም አቀፍ የልማት ሥራዎች በተሳለጠ መንገድ ለማቅረብ የሚያስችል በጀት መሆኑም ተገልጿል። ከፍተኛ ድርሻ የያዘው የካፒታል በጀቱ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለቤት ልማት፣ ለመሠረተ ልማት ግንባታ፣ የትራንስፖርት አገልግሎትን ማሻሻልና አጠቃላይ የከተማዋን ልማትና ዕድገት ይበልጥ ለማዘመን የተመደበ እንደሆነ ተገልጿል።
የኩታገጠም እርሻ የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ የገጠር ትራንስፎርሜሽንን እያፋጠነ ነው
Jul 13, 2026 462
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የኩታገጠም የግብርና እርሻ ሥርዓት የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ የገጠር ትራንስፎርሜሽንን እያፋጠነ መሆኑን የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) ገለጹ። ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፥የገጠር ትራንስፎርሜሽን ስትራቴጂው የአርሶ አደሩን የግብርና ሥርዓት በማዘመን፣ዘላቂ የምርታማነት ምኅዳር በመፍጠር ላይ ይገኛል። የኢትዮጵያ የግብርና ምርታማነት አድማስ እየሰፋ መምጣቱ ለምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥና ለገጠር ትራንስፎርሜሽን መፋጠን ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም አንስተዋል።   ይህም የግብርናውን ዘርፍ ከባህላዊ አሠራር በማላቀቅ አዳዲስ አማራጮችን በመፍጠርና ሜካናይዜሽንን በማስፋፋት የአርሶ አደሩ ተጠቃሚነትና የኑሮ ደረጃ ላይ ከፍተኛ መሻሻል እያመጣ መሆኑን አስረድተዋል። የኩታገጠም የግብርና አሠራርና የሜካናይዜሽን ሥርዓት መተግበር የሰብል ምርታማነትን በብዛትና በጥራት ለማሳደግ ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ቀደም ሲል በአመት አንድ ጊዜ ብቻ ይታረስ የነበረው መሬት አሁን ላይ በበጋ መስኖና በተለያዩ የምርታማነት ወቅቶች ታግዞ ምርታማነቱን ማሳደግ እያስቻለ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት፣የሀገሪቱን የምግብ ፍጆታ በማሟላት አልፎም ለውጭ ገበያ መቅረብ የሚችልበትን አስተማማኝ መዋቅራዊ የስኬት ሽግግር ማስመዝገቡን አብራርተዋል።   የኩታገጠም ዘመናዊ አስተራረስ ዘዴም የሚታረስን መሬት በማስፋትና አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለገበያ የሚያቀርብበትን አቅም በመፍጠር የገጠር ኢኮኖሚን እያነቃቃ ነው ብለዋል። ይህ አሠራር ለግብርና ምርቶች እሴት በመጨመር ረገድ በሚደረጉ ጥረቶች ታግዞ የገጠር ሽግግርን ከማፋጠን ባሻገር የሥራ ዕድል በመፍጠርና ለኢንዱስትሪ ልማት ግብዓት በማቅረብ ረገድ አመርቂ ውጤቶችን እያስመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል።   የኩታገጠም የግብርና አስተራረስና የሜካናይዜሽን ሥርዓት መዘርጋት የኢትዮጵያን የግብርና ዘርፍ ወደ ዘመናዊ ምዕራፍ በማሸጋገር የምግብ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥና የዜጎችን ተጠቃሚነት የማሳደግ ጉዞን እያፋጠነ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ባለፉት ዓመታት በከተማዋ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡና ገጽታንም በእጅጉ የለወጡ ናቸው
Jul 13, 2026 146
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦ባለፉት ዓመታት በአዲስ አበባ ከተማ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡና ገጽታን በእጅጉ የለወጡ መሆናቸውን የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አባላት ገለጹ፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት በአዲስ አበባ ከተማ በማህበራዊ፣ በኢኮኖሚ እና በፖለቲካ የተመዘገቡ ስኬቶችን አስመልክቶ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባላት ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በቆይታቸውም ባለፉት ዓመታት አዲስ አበባን የለወጡ እጅግ አስደማሚ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል አለማየሁ አረዳ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የተከናወኑት የልማት ሥራዎች እጅግ ስኬታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከተማዋን ወደ ላቀ ደረጃ የለወጡና ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ዘርፈ ብዙ ስራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም በአስፈጻሚው አካልና በምክር ቤቱ መካከል የነበረው ግንኙነት እጅግ ጤናማና መልካም የሥራ ባህል የነበረው መሆኑን አብራርተዋል። ይህ አዎንታዊ አሠራርና መልካም ባህል በቀጣዩ ምክር ቤትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ያላቸውን ትልቅ ተስፋ ገልጸዋል።   ሌላኛዋ የምክር ቤት አባል ደብረሲና ሙሴ በበኩላቸው ያለፉት አምስት ዓመታት ለምክር ቤቱ አዲስ የሥራ ምዕራፍና ስኬት የታየበት ወቅት እንደነበር ገልጸዋል። በዚህ ጊዜ ውስጥ የተከናወኑት የማህበራዊ ዘርፍ ሥራዎች በግልጽ በአይን የሚታዩና የሕዝብን የኑሮ ፍላጎት በአግባቡ የመለሱ መሆናቸውን አስረድተዋል። ነባር የጤና ተቋማት እንዲስፋፉና አዳዲስ ዘመናዊ ተቋማት እንዲገነቡ መደረጉ እንዲሁም፤ የትምህርት ተደራሽነትና የተማሪዎች ቅበላ እንዲጨምር ምክር ቤቱ ጠንካራ ግፊት ሲያደርግ መቆየቱንና አስፈጻሚው አካልም በዚህ ልክ የተሻሉ ሥራዎችን ማከናወኑን ጠቅሰዋል። ምክር ቤቱ የሕዝብ ድምፅ በመሆን ለነዚህ መልካም ሥራዎች ጠንካራ መሠረት መጣሉን የገለጹት አባልዋ ቀጣዩ ምክር ቤትም የተጀመረውን የልማት ጉዞ አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አሳስበዋል።   የምክር ቤት አባሉ ኢቲሳ ደሜ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ያለፉት አምስት ዓመታት በሁሉም ዘርፎች ፈጣን ለውጥ የታየበት ወቅት እንደነበር ገልጸዋል። በጤናው ዘርፍም ዘመናዊ ማሽነሪዎች የተሟሉላቸው ሆስፒታሎች መገንባታቸው ቀድሞ ወደ ውጭ አገር የሚደረጉ የሕክምና ጉዞዎችን እንደሚያስቀርና በትምህርትም ዘርፍ የተማሪዎች ውጤት በከፍተኛ ሁኔታ እየተሻሻለ መምጣቱን ገልጸዋል። የተጀመሩት አበረታች የልማትና የፖለቲካ ስኬቶች ቀጣይነት ሊኖራቸው እንደሚገባ አሳስበዋል። በመሆኑም የሚቀጥለው ምክር ቤት የተጀመሩትን ፈጣን የልማት ሥራዎች በቁርጠኝነት ይዞ መስራትና ህብረተሰቡን በታማኝነት ማገልገል እንዳለበት ጥሪያቸውን አቅርበዋል።   የምክር ቤት አባሉ አባወይ ዮሐንስ እንደገለጹት ባለፉት አመታት ከተማዋን ለነዋሪዎቿ ምቹና ተወዳዳሪ ከማድረግ አንፃር ማህበረሰቡን መሰረት ያደረጉና የልማት ጥያቄዎችን በተግባር የመለሱ ሰፋፊ ፕሮጀክቶች ተተግብረዋል። ነዋሪዎች ቀድሞ ሩቅ ቦታ ሄደው የሚያዩትንና የሚመኙትን ዘመናዊ የከተማ አኗኗር፣ በአካባቢያቸው ማግኘት መቻላቸው የፕሮጀክቶቹን የሕዝብ ተጠቃሚነት ማረጋገጫ ነው ብለዋል። በተጨማሪም በጤና እና በትምህርት ዘርፍ አበረታች ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቁመዋል።    
የገበያ ማዕከላት መስፋፋት የዋጋ ንረትን ለመቀነስና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማግኘት ወሳኝ መፍትሔ ሆነዋል -ሸማቾች
Jul 13, 2026 222
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦ የገበያ ማዕከላትና የቅዳሜና እሁድ ገበያ መስፋፋት የዋጋ ንረትን ለመቀነስና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማግኘት ወሳኝ መፍትሔ እንደሆኗቸው ሸማቾች ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በሰጡት ማብራሪያ መንግሥት የኑሮ ውድነትንና ገበያን ለማረጋጋት በርካታ እርምጃዎችን እየወሰደ ይገኛል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ መንግሥት የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት በርካታ እርምጃዎችን እየወሰደ ይገኛል። ከተወሰዱ ቀዳሚ እርምጃዎች መካከል የሸማቾችን አማራጭ ማሳደግ አንዱ ሲሆን፣ በዚህም የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ተደራሽነት ከ2ሺህ በላይ ማድረስ መቻሉን አስታውቀዋል።   የገበያ ማዕከላት የከተማዋን የኑሮ ውድነት ለማረጋጋት እንደ ዋነኛ መፍትሔ የሚያገለግሉ ሲሆን እነዚህ ማዕከላት የግብርና ምርቶችን በቀጥታ ከአምራች ወደ ሸማች በማገናኘት፣ በመካከል የሚፈጠረውን የዋጋ ጭማሪ በመግታት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለሕዝብ ተደራሽ ያደርጋሉ። ለኅብረተሰቡ የሚሰጡት አገልግሎትም ከፍ ያለ ነው፤ ነዋሪዎች የተለያዩ የፍጆታ ዕቃዎችን በአንድ ቦታ በመሸመት ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን ይቆጥባሉ፤ በተለይም በአቅራቢያቸው በመገንባታቸው የትራንስፖርት ወጪን በማስቀረት የኑሮ ጫናን በእጅጉ ያቀላሉ።   ይህም ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ከመግዛት ባሻገር፣ በገበያ ውስጥ የሚታየውን የዋጋ አለመረጋጋት በመከላከል ለኅብረተሰቡ ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ እፎይታ ይፈጥራል።     አቶ ሄኖክ ተወልደ እና አቶ ረታ አክሊሉን ጨምሮ ሌሎች አስተያየት ሰጪዎች እንደገለጹት፣ እነዚህ ማዕከላት ተጨማሪ የትራንስፖርት ወጪን በማስቀረት የቤተሰብ ፍጆታዎችን በቀላሉ ለመሸመት ምቹ ሁኔታን ፈጥረዋል።   የመንግሥትን የገበያ ማረጋጋት ጥረቶችን አድንቀው ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም ጠቅሰዋል፡፡ ሌላዋ አስተያየት ሰጪ ኤልሳ ተሰማ እንደጠቆሙት፣ በምርቶች ላይ የሚስተዋለውን የዋጋ አለመረጋጋት ለመፍታት እነዚህን ማዕከላት ይበልጥ ማጠናከርና ማስፋፋት ይገባል። መንግሥት ለዚህ ተግባር ልዩ ትኩረት በመስጠት የኑሮ ጫናውን ለማቃለል የሚያስችሉ ውሳኔዎችን ይበልጥ ማጠናክር እንደሚገባው ጠቅሰው ይህን የመሰለ የህዝብ ተጠቃሚነትን ያማከለ ሂደት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አሳስበዋል። ከዚህ ጎን ለጎን መንግሥት የምርት አቅርቦትን ለመጨመር የተረጋጋ የገበያ ሥርዓት ለመገንባት የጀመረውን ጥረት ማጠናከር እንዳለበት ጠቅሰው የአቅርቦት ሰንሰለቱን ይበልጥ የማዘመን እርምጃ መወሰድ እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡   አዲስ አበባ ንግድ ቢሮ ኃላፊ ኃቢባ ሲራጅ በበኩላቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ ኅብረተሰቡ ልዩ ልዩ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ አምራቾችና አቅራቢዎች ምርቶቻቸውን በቀጥታ የሚያቀርቡበትን ምቹ ሁኔታ የመፍጠር ሥራ በትኩረት እየሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በተጨማሪም የንግድ ሰንሰለቱን በማናጋት በሸማቹና በአምራቹ ላይ ጫና የሚፈጥሩ ሕገ-ወጥ ደላሎችን ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመው፣ ይህ የቁጥጥርና የሕግ ማስከበር ሥርዓት ይበልጥ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። መንግሥት በቀጣይም የኅብረተሰቡን የኑሮ ጫና የሚያቃልሉ የልማት ተግባራትን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል፡፡        
የኢትዮጵያ የእንስሳት ሃብት ልማት የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት በማሻሻል ውጤት እያስገኘ ነው
Jul 13, 2026 209
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የእንስሳት ሃብት ልማት የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት በማሻሻል ውጤት እያስገኘ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የግብርና ሚኒስቴር ከአፍሪካ ህብረት የአህጉር-አቀፍ የእንስሳት ሃብት ቢሮ ጋር በመተባበር የተዘጋጀ ጉባኤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ፎረሙ በአፍሪካ የእንስሳት ሃብት ልማትን በማጎልበት የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችል፣ አርብቶ አደሮች የተሻለ ገበያ እንዲያገኙና የሀገራትን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የፖሊሲ አቅጣጫ ለማስቀመጥ ያለመ ነው። ኢትዮጵያ የእንስሳት ሃብት ልማትን በማሳደግ የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተጨባጭ እርምጃዎችን በመውሰድ እየሰራችበት መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም አርሶና አርብቶ አደሮች የሚያጋጥሟቸውን የውሃና የመኖ እጥረት በዘላቂነት የሚቀርፉ እንዲሁም የእንስሳት ሕክምና መስጫ ተቋማትን የማስፋፋት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከአርብቶ አደሮች ጋር የሚሰሩ ተቋማትን፣ የእንስሳት ገበያ ማእከላትን ለአርብቶ አደር አካባቢዎች ተደራሸነት የማጠናከር ስራዎችንም እየተሰራበት እንደሆነም አብራርተዋል። በአፍሪካ ህብረት የእንስሳት ሀብት ቢሮ ዳይሬክተር ሁያም ሳሊህ (ዶ/ር) አፍሪካ የዓለምን የእንስሳት ሃብት ከፍተኛ ድርሻ ብትይዝም፣ ከእሴቱ ግን የምታገኘው በጣም አነስተኛ ነው ብለዋል። በቀጣይም የአህጉሪቷን ግዙፍ የእንስሳት ሃብት በማልማት የአርሶና አርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማሻሻል በሁሉም ዘርፍ የኢንቨስተመንት አማራጮችን ማስፋት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
በኦሮሚያ ክልል የግብርናውን ዘርፍ ለማሳደግ የተተገበሩ አሰራሮች ውጤት አስገኝተዋል
Jul 13, 2026 222
አዳማ፤ ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ በግብርና ዘርፍ የተተገበሩ አሰራሮች ውጤት ማስገኘታቸውን የክልሉ ፕላንና ልማት ኮሚሽን ኮሚሽነር አብዲ ያዩ (ዶ/ር) ገለፁ። የክልሉ የመንግሥትና የፓርቲ የ2018 በጀት ዓመት የኢኮኖሚ ዘርፍ የሥራ አፈጻጸም ግምገማ እየተካሄደ ይገኛል።   በግምገማው መድረክ ላይ ዝርዝር ሪፖርት ያቀረቡት የክልሉ ፕላንና ልማት ኮሚሽነር አብዲ ያዩ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ በክልሉ የግብርናውን ዘርፍ ምርታማነት ለማሳደግ የተተገበሩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችና የተደረጉ ሁለንተናዊ ድጋፎች ከፍተኛ ውጤት አስገኝተዋል። ለዚህም ማሳያ የሚሆነው በከተሞችና በገጠር አካባቢዎች የወተት ላሞች እርባታ በዘመናዊ መንገድ መተግበሩና ምርጥ የእርባታ ዶሮዎች ለአርሶ አደሩ መሰራጨታቸው መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም በዓሣ እርባታ ዘርፍ ከ1 ነጥብ 9 ሚሊዮን በላይ የዓሣ ጫጩቶች ለአርሶ አደሩና ለአርብቶ አደሩ ተሰራጭተው ወደ እርባታ ኩሬዎች መግባታቸውን ገልጸዋል። የአርሶ አደሩን የሰብል ልማት ውጤታማነት በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና በቅርበት የገበያ ትስስር የሚያገኝበት ምቹ የገበያ ማዕከላት መገንባታቸውን ኮሚሽነሩ ጠቅሰዋል። ይህም የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ከማሳደጉ ባለፈ፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራና የኑሮ ውድነትን ለመቋቋም ትልቅ እገዛ ማድረጉን አስረድተዋል። በክልሉ የሚታየውን የሥራ አጥነት ችግር ለመቅረፍ በተደረገው ሰፊ ጥረትም በበጀት ዓመቱ ከ2 ነጥብ 7 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አዲስ የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል ብለዋል። የክልሉን ሁለንተናዊ ልማት በራስ አቅም ለመሸፈን በተደረገው የውስጥ ገቢ ማሰባሰብ ጥረትም የተሻለ ገቢ መሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል።   በበጀት ዓመቱ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት በተደረገው የተቀናጀ ጥረት 13 ሺህ 147 አዳዲስ አልሚ ባለሀብቶችን መሳብ ተችሏል ነው ያሉት። ይህንን ተግባር ይበልጥ ለማስቀጠልም አርሶ አደሮችና የአገር ውስጥ አንቀሳቃሾችን በመደገፍ፣ ሀብት አፍርተው ከእርሻ ሥራ ወደ ኢንቨስትመንት ባለቤትነት እንዲሻገሩ መደረጉን ጠቅሰዋል። የሕዝቡን የማኅበራዊ አገልግሎት ተደራሽነት ለማረጋገጥ በተደረገው ጥረትም በትምህርት፣ በጤና፣ በንጹህ መጠጥ ውኃና በመንገድ ልማት ዘርፎች እጅግ የተሻለና አበረታች አፈጻጸም መመዝገቡን አንስተዋል። በአዳማ ከተማ አባ ገዳ አዳራሽ እየተካሄደ ያለው ይህ የመንግሥትና የፓርቲ የሥራ አፈጻጸም ግምገማ በቀጣዮቹ ቀናትም እንደሚቀጥል ከወጣው መርሃ ግብር ለማወቅ ተችሏል።
በአማራ ክልል ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል
Jul 13, 2026 176
ባህር ዳር ፤ ሐምሌ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል በመፍጠር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን የማረጋገጥ ስራ መከናወኑን የክልሉ ስራና ክህሎት ቢሮ ገለፀ። በክልሉ ለስራ ዕድል ፈጠራ የሚያገለግሉ ፀጋዎችን በመለየት ለወጣቶች የስራ ዕድል በመፍጠር የኢኮኖሚ አቅማቸውን የማሳደግ ስራ እየተሰራ ይገኛል። የቢሮው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ አንዳርጋቸው ጎፋ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በግብርና፣ በኢንዱስትሪና በአገልግሎት ዘርፎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል ለመፍጠር ተችሏል።   በዚሁ ወቅት የስራ እድል ፈጠራዉን ስኬታማ ለማድረግ በቅንጅት የሚመራ ግብረ ኃይል በማቋቋም እና አጋር ተቋማትን በማቀናጀት ሰፊ ስራ መከናወኑን ጠቅሰዋል። በዚህም ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ወገኖች የስራ ዕድል በመፍጠር የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ማረጋገጥ መቻሉን ገልፀዋል። ከተፈጠረው የስራ እድል ውስጥም 75 በመቶ በቋሚነት የተፈጠረ ሲሆን ከዚህ ውስጥም 50 በመቶ የሚሆኑት ሴቶች መሆናቸውን ነው የተናገሩት። የስራ ዕድሉ በመስኖ እና በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት፣ በእንስሳት እርባታና ማድለብ፣ በጨርቃጨርቅና አልባሳት እንዲሁም በእንጨትና ብረታብረት ስራዎች የተፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። በዚሁ ወቅት በስራ እድሉ ተጠቃሚ የሆኑ ዜጎች የገንዘብ እጥረት እንዳይገጥማቸው ለማድረግ በተከናወኑት ተግባራትም 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ከተለያዩ አበዳሪ ተቋማት እንዲያገኙ ተደርጓል ነው ያሉት።   በተጨማሪም 21 ሺህ 400 ሄክታር የሚጠጋ መሬትና ከ 2 ሺህ 200 የሚበልጡ የመስሪያና የመሸጫ ሼዶች ተገንብተው የስራ እድል ለተፈጠረላቸው ዜጎች ማስተላለፍ መቻሉን ገልፀዋል። ኢንተርፕራይዞቹ የገበያ ትስስር ተጠቃሚ እንዲሆኑ በተከናወኑት ተግባራትም የ8 ነጥብ 3 ቢሊዮን የሀገር ውስጥ፤ ከ1 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ሃገራት የገበያ ትስስር መፈጠሩንም አብራርተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም