ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የክልሉን የልማት አቅም በመጠቀም የመሰረተ ልማት ችግሮችን ደረጃ በደረጃ በመፍታት ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ እየተሰጠ ነው
Feb 12, 2026 89
ታርጫ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልልን የልማት አቅም በመጠቀም የመሰረተ ልማት ችግሮችን ደረጃ በደረጃ በመፍታት ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ እየተሰጠ ነው ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለፁ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 9ኛ መደበኛ ጉባኤውን በታርጫ ከተማ እያካሄደ ይገኛል። በዛሬው ውሎው የምክር ቤት አባላቱ በልማት፣ በሰላምና በመልካም አስተዳደር ዘርፎች በተደረገ ሰፊ ጥረት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተዋል። በተለይም ያደሩና የቆዩ የውሃ፣ የድልድይ፣ የመንገድና ሌሎች የመሰረተ ልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ የተደረገው ሰፊ ርብርብ የሚበረታታና ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት መሆኑንም ገልፀዋል።   የክልሉ መንግስት የመሰረተ ልማት ችግሮችን ለመፍታት ያከናወናቸው ተግባራት የሚበረታቱ መሆኑን አባላቱ ጠቅሰው የገጠር ተደራሽ መንገዶችና ድልድዮች ግንባታ ላይ ትኩረት እንዲደረግም ጠይቀዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ ፤ ክልሉ ያለውን አቅም በመጠቀም ቅድሚያ የሚሰጣቸውን የመሰረተ ልማት ችግሮች ደረጃ በደረጃ በመፍታት ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ እየተሰጠ ነው ብለዋል። ለዚህም በመንገድና ድልድይ መሰረተ ልማት ግንባታ ሂደት ውስጥ የማህበረሰቡ ተሳትፎና ድርሻ ትልቅ አቅም መሆኑን አንስተው ይህም ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል። ግንባታቸው በፌደራል መንግስት እየተከናወኑ የሚገኙ የአስፋልት መንገዶች እንዲፋጠኑ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅርበት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።   በግብርናው ዘርፍም የምርጥ ዘር አቅርቦትን በማሻሻል ውጤታማ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፣ የህብረት ስራ ማህበራትን አቅም የማጠናከር ስራም ትኩረት እንደሚሰጠው ጠቁመዋል። በክልሉ ከኮሪደር ልማት ጋር በማያያዝ ዘመናዊ ከተሞችን ለመፍጠር በሰፊው እየተሰራ መሆኑን አመልክተው መሰረተ ልማትን በማሟላትና በማስተር ፕላን የሚመሩ ከተሞችን እውን ከማድረግ አኳያ ስራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል። ከማዘጋጃ ቤት፣ ከንግድና ከገቢ ጋር የሚገናኙ አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝ በማድረግ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የመሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎትን ለማስፋት የተጀመረው ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
በሀገሪቱ የቡና ምርት ጥራት ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የቅምሻ ባለሙያዎችን ማፍራት ላይ ትኩረት ተደርጓል
Feb 12, 2026 58
ሀዋሳ ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦በሀገሪቱ የቡና ምርት ጥራት ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የቅምሻ ባለሙያዎችን ማፍራት ላይ ትኩረት መደረጉን የኢትዮጵያ ምርት ገበያ አስታወቀ። ምርት ገበያው ዘመናዊና ጥራት ላይ ያተኮረ ግብይትን ለማሳለጥ ያለመ የሰው ኃይል ለማፍራት አካዳሚ ከፍቶ እየሰራ ነው። ዛሬ በሀዋሳ ማዕከል የተጀመረው የመጀመሪያ ዙር ስልጠናም የቡና ቅምሻ ደረጃ አወጣጥ ላይ ማተኮሩ ተመልክቷል። የምርት ገበያው አካዳሚ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰለሞን ተሾመ፤ ምርት ገበያው ቡናን ጨምሮ የግብርና ምርቶች ግብይትን በማዘመን ጥራታቸውን እንዲጠብቁ ለማድረግ ለክህሎት ስልጠና ትኩረት በመስጠት እየሰራ ነው ብለዋል። በዚህም የቡና መገኛ የሆነችው ኢትዮጵያ የሚገባትን ለማግኘት፣ በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነቷን ለማጠናከርና የምርት ሂደቱ የጥራት ደረጃውን እንዲጠብቅ ለማድረግ በዕውቀት የሚሰራ የሰው ኃይል ለማፍራት ጥረት እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። የዓለም አቀፍ ገበያው የሚፈልገውን የጥራት ደረጃ የሚመጥን ምርት ለማውጣትና በድህረ ምርት ሂደት ላይ የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለመቅረፍ በክህሎት የዳበረ የሰው ሀይል ማብቃት አስፈላጊ መሆኑን አመልክተዋል።   መሰል ስልጠና በአዲስ አበባ ማእከል ከተጀመረ ሶስት ዓመታት እንዳስቆጠረ ገልፀው በዚህም 480 ባለሙያዎች መሰልጠናቸውንና ስልጠናውን በማስፋት ዛሬ በሀዋሳ መጀመሩንም ጠቁመዋል። ሀገሪቱ ከወጭ ንግድ የሚገባትን እንድታገኝ በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ሀይል ማፍራት እንደሚገባ የገለጹት ደግሞ በምርት ገበያው የሀዋሳ ቅርንጫፍ ስራ አስኪያጅና የቡና ጥራት ባለሙያ አቶ ነቢያት ጀማል ናቸው። የሀዋሳ ስልጠና ማዕከልም በመጀመሪያው ዙር 27 ሰልጣኞችን ተቀብሎ በቡና ምርት ጥራት ማስጠበቅ ላይ የክህሎት ስልጠና እየሰጠ ነው ብለዋል። ከሰልጣኞች መካከል ከኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ጉጂ ዞን ሀምበላዋመና ወረዳ የመጡት አቶ ድልነሣ አያልነህ፤ በቡና ልማት ዘርፍ ልምዱ ያላቸው ቢሆንም ከጥራት አንጻር የሚነሳውን ችግር ለመፍታት በስልጠናው እየተሳተፉ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በተለይም በምናመርተው ልክ ተጠቃሚ ለመሆን የዓለም አቀፍ ገበያው የሚፈለገውን ጥራት ደረጃ ማሟላት ይገባል ያሉት ሰልጣኙ ለዚህ ደግሞ የምርት ገበያው የጀመረው ስልጠና ክህሎታቸውን በማዳበር እንደሚያግዛቸው ገልጸዋል።
የአፍሪካን የውሃ ሃብት ፍትሐዊ ተጠቃሚነት በማስፈን የአህጉሪቷን ዕድገት ማሳለጥ ያስፈልጋል 
Feb 12, 2026 63
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦የአፍሪካን የውሃ ሃብት ፍትሐዊ ተጠቃሚነት በማስፈን የአህጉሪቷን ዕድገት ማሳለጥ እንደሚያስፈልግ የሌሴቶ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ማኩጆ ገለጹ። 48ኛው የአፍሪካ ሕብረት የሥራ አስፈፃሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ በአዲስ አበባ ለሁለት ቀናት ሲካሄድ ቆይቶ ተጠናቋል። በስብሰባው ላይ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የአንጎላ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የሥራ አስፈፃሚ ምክር ቤት ስብሳቢ ሊቀ መንበር አምባሳደር ቴቴ አንቶኒዮ እና የአባል ሀገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ተሳትፈዋል። በመደበኛ ስብሰባው የተሳተፉት የሌሴቶ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጆን ማኩጆ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ሌሴቶ በደቡባዊ አፍሪካ ቀጣና ዜጎችን በንጹህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚነት ማስተሳሰር የሚያስችል አቅም አላት። የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት ጉባዔ በዘላቂ ውሃ ልማትና ንጽህና አጠባበቅ ላይ ትኩረት ማድረጉ የውሃ ሃብት አስተዳደርና ተደራሽነትን በማስፋት አጀንዳ 2063 እውን ለማድረግ አቅም እንደሚሆን ገልጸዋል። የሌሶቶ ዋና ዋና ወንዞችም ለደቡብ አፍሪካ፣ ቦትስዋና፣ ናሚቢያና ሌሎች የደቡብ አፍሪካ ቀጣና ሀገራት የንጹህ መጠጥ ውሃ የማቅረብ አቅም ያላቸው መሆናቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም በአፍሪካ ሕብረት የ2026 የውሃና የንፅህና አጠባበቅ በተቀመጠው መሪ ሃሳብ መሰረት ከቀጣናው ሀገራትና ዓለም አቀፍ የልማት አጋሮች ጋር በትብብር እንደሚሰሩ አንስተዋል። ሌሴቶ ለቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ ትብብር መጠናከር በቁርጠኝነት የምትሰራ ሀገር መሆኗን አስረድተዋል። ለዚህም የሁሉም ድምጽ በፍትሐዊነት የሚሰማበት ጠንካራ የባለብዙ ወገን ሥርዓት ለማጎልበት በቅንጅት እየሰራች መሆኗን አብራርተዋል። የአፍሪካ የውሃ ሃብት ለአህጉሪቷ ዕድገት ወሳኝ ናቸው ያሉት ሚኒስትሩ፤ ለዚህም የአፍሪካን የውሃ ሃብት ፍትሐዊ ተጠቃሚነት በማስፈን የአህጉሪቷን ዕድገት ማሳለጥ ያስፈልጋል ብለዋል። 39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባዔ "ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚል መሪ ሀሳብ ይካሄዳል ።
በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረጉ የልማት ኢኒሼቲቮች ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ ጀምረዋል 
Feb 12, 2026 74
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረጉ የልማት ኢኒሼቲቮች ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ መጀመራቸውን የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንትና የዋና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አደም ፋራህ ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ እና የመንግሥት የ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ድጋፋዊ ሱፐርቪዥን ማጠቃለያ መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንትና የዋና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አደም ፋራህን ጨምሮ፣ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም የሱፐርቪዥን ቡድኑ አባላት ተገኝተዋል። በመድረኩ ላይ የሱፐርቪዥን አባላቱ በክልሎችና በሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች ባደረጉት ድጋፋዊ ሱፐርቪዥን ያገኟቸውን ውጤቶችና ተሞክሮዎች አቅርበዋል። በዚህም መንግስት ተግባራዊ ያደረጋቸው የልማት ኢኒሼቲቮች የሕዝብን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ውጤት እያስመዘገቡ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በተለይም ተረጂነትን ለማስቀረት፣ የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ፣ በልማት ስራዎች፣ በግብርና ልማት፣ በኮሪደር ልማት፣ ከቴክኖሎጂ ሽግግር እና ከኢንዱትሪያላይዜሽን እንዲሁም ከሌሎች አኳያ ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸው ተጠቅሷል። በዚህ ወቅት የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ እንደተናገሩት፤ የዚህ ሱፐርቪዥን ዋነኛ ዓላማ በከፍተኛ አመራሮች ስልጠና ማጠቃለያ ላይ የተቀመጡ አቅጣጫዎችና የሥራ መመሪያዎች አፈጻጸም መገምገም ነው።   "በመደመር መንግሥት ዕይታ፣ የዘርፎች እመርታ" በሚል መሪ ሀሳብ በተሰጠው ስልጠና ማጠናቀቂያ ላይ ሀገራዊ ትኩረት በሚሹ ጉዳዮች ላይ የተሰጡ ዝርዝር መመሪያዎች መሬት ላይ የወረዱበትን ሁኔታ ሱፐርቪዥኑ በዝርዝር መመልከቱንም ተናግረዋል። በዚህም በክልሎችና በሁለቱም የከተማ አስተዳደሮች በተደረገው ምልከታ፤ መንግሥት ተግባራዊ ያደረጋቸው የልማት ኢኒሼቲቮች የሕዝብ ተጠቃሚነትን ከማረጋገጥ አኳያ አበረታች ውጤት እያስመዘገቡ መሆኑ መታየታቸውን ገልጸዋል። በተለይም ተረጂነትን ለማስቀረት፣ የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ የተጀመሩ ጥረቶች፣ በግብርና፣ በኮሪደር ልማትና በኢንዱስትሪያላይዜሽን ዘርፎች የታዩ ውጤታማ ሥራዎች፣ ከቴክኖሎጂ ሽግግርና ከሌሎች የልማት ስራዎች አኳያ የተከናወኑ ተግባራት አበረታች መሆናቸውን ጠቅሰዋል።   የሱፐርቪዥን ቡድኑ የተሰጠውን ተልዕኮ በውጤታማነት ማከናወኑን ጠቅሰው፤ ስራዎች ከዕቅድ ባለፈ በተግባር መሬት ላይ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት መጀመራቸው የታየበት ትልቅ ግብዓት የተገኘበት ሂደት መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይ በክልሎች መካከል የሚታየውን የአፈጻጸም ልዩነት ለማቀራረብና ተመሣሣይ ውጤት እንዲመዘገብ ለማድረግ በትኩረት እንደሚሠራ ገልጸዋል። የአፈጻጸም ልዩነትን ለማቀራረብ ሦስት ዋና ዋና ስልቶች እንደሚተገበሩ ጠቁመዋል። በዚህም ለጉዳዮች ባለቤት የማበጀት ተግባር እንደሚከናወን ጠቁመው፤ ተቋማት እንደየሥራ ባሕሪያቸው የወረዱ የልማት ኢኒሼቲቮችን ውጤታማነት የማረጋገጥ ኃላፊነት እንዲወስዱ ይደረጋል ብለዋል። የተቋማትን ቅንጅት ማጠናከርም ሌላኛው ስልት መሆኑን ጠቅሰው፤ በሁሉም ኢኒሼቲቮች ላይ የተናበበ አሰራር እንዲኖር እንደሚሰራ አብራርተዋል። በተመሣሣይ ቀጣይነት ያለው ድጋፍና ክትትልን በማጠናከር አፈጻጸምን የመከታተል፣ ስታንዳርድ የማበጀትና ማነቆዎችን የመፍታት ሥራ እንደሚከናወን ጠቁመዋል። በክልሎች ባላቸው ጸጋ ልክ ሥራዎችን እንዲተገብሩና የሕዝብን ተጠቃሚነት እንዲያረጋግጡ የክትትልና የግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስገንዝበዋል።
በከተማዋ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ባለፉት ስድስት ወራት 14 ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ ገብተዋል
Feb 12, 2026 63
ባህር ዳር፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦በባህር ዳር ከተማ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ 14 ኢንዱስትሪዎች ወደ ምርት መግባታቸውን የከተማዋ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ አስታወቀ። የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች፣ የአስተዳደሩ ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በባህር ዳር ከተማ ወደ ሥራ የገቡ ኢንዱስትሪዎችን የሥራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የከተማ አስተዳደሩ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ሃላፊ ብርሃን ንጉሴ፤ የ“ኢትዮጵያ ታምርት እኛም እንሸምት” ንቅናቄ የከተማዋን የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ማነቃቃቱን ተናግረዋል።   ንቅናቄውን ተከትሎ ባለፉት ስድስት ወራት ለኢንዱስትሪዎች በተደረገ ድጋፍና ክትትል 14 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት መግባታቸውን ገልጸዋል። በባህር ዳር ከተማ 73 ነባርና አዲስ ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርት ላይ አተኩረው እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰው፣ ኢንዱስትሪዎቹ ባለፉት ስድስት ወራት ከ66 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማዳን ችለዋል ነው ያሉት። በከተማዋ አራት ኢንዱስትሪዎች ምርቶቻቸውን በቀጥታ ወደ ውጪ በመላክ ከ3 ነጥብ 1ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ገቢ ማስገኘታቸውንም የመምሪያ ሃላፊዋ አመልክተዋል።   እንደሃላፊዋ ገለጻ፤የኢትዮጵያ ታምራት ንቅናቄ የከተማዋን የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ከማነቃቃት በላይ ከ2 ሺህ 400 ለሚልቁ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ አስችሏል። በከተማዋ አጠቃላይ 273 ኢንዱስትሪዎች በማምረት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው መንግስት ለኢንዱስትሪዎቹ ድጋፍና ክትትል እያደረገ መሆኑን አረጋግጠዋል። የኤም.ኤስ.ሲ ቢዝነስ ግሩፕ የባህር ዳር ቀጣና ሥራ አስኪያጅ አበረ አበራ በበኩላቸው እንዳሉት፤ ፋብሪካው በእንስሳት መኖ ማቀነባበሪያና በምግብ ዘይት ማምረት ላይ ተሰማርቶ እየሰራ ይገኛል።   ፋብሪካው በቀን እስከ 200 ሺህ ሊትር የምግብ ዘይት የማምረት አቅም እንዳለውና በአሁኑ ወቅትም ተኪ ምርት በማምረት የውጭ ምንዛሬን በማስቀረት በኩል የድርሻውን እየተወጣ ይገኛል ብለዋል።   በከተማ አስተዳደሩ እየተደረገላቸው ያለው ክትትልና ድጋፍ የሚያስመሰግንና ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት ነው ያሉት ደግሞ የአማጋ ባህር ዳር ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ አማረ መብራቴ ናቸው።
የተደረገልን የኢንቨስትመንት ማበረታቻ ለተሻለ ሥራ የሚያነሳሳን ነው - አርሶ አደሮች 
Feb 12, 2026 90
ሮቤ ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦በባሌ ዞን የተደረገላቸው የኢንቨስትመንት ማበረታቻ ለተሻለ ሥራ እንደሚያነሳሳቸው ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት በመሸጋገር እውቅና ያገኙ አርሶ አደሮች ገለጹ። በባሌ ዞን ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት ለተሸጋገሩ 301 አርሶ አደሮች እና ማህበራት የኢንቨስትመንት ፍቃድ መስጠቱንም የዞኑ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽህፈት ቤት ገልጿል።   አርሶ አደር ኡመር አህመድ ባለፉት ዓመታት በተሰማሩበት የግብርና መስክ ውጤታማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት ከተሸጋገሩ አርሶ አደሮች መካከል አንዱ ናቸው፡፡   አርሶ አደሩ በስንዴና ሌሎች ሰብሎች ሽያጭ ውጤታማ በመሆን 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር አስመዝግበው በዛሬው እለት ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ነው የሚገልጹት። በአሁኑ ወቅትም በግብርና የኢንቨስትመንት አማራጮች ለመሰማራት ሶስት ሄክታር የኢንቨስትመንት መሬትን በማበረታቻነት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። በተሰማሩበት የአትክልትና ፍራፍሬ ልማትና ሽያጭ ስራ 1 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር ካፒታል በማስመዝገብ ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን የገለጹት ደግሞ የደሎ መና ወረዳ አርሶ አደር አብዱልከሪም ኢብራሂም ናቸው።   በአሁኑ ወቅት ከተሰጣቸው የእውቅና ሰርተፊኬት ባሻገር በኢንቨስትመንት ማበረታቻነት 10 ሄክታር የመሥሪያ ቦታ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። አርሶ አደሮቹ እንዳሉት የተደረገላቸው ዕውቅናና የኢንቨስትመንት ማበረታቻ መሬት በቀጣይ የተሻለ ሥራ ለመሥራት የሚያነሳሳ ነው ይላሉ። የዞኑ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መሐመድ ኢብሮ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በዞኑ 301 አርሶ አደሮች እና የጥቃቅንና አነስተኛ ማህበራት ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት ተሸጋግረዋል።   አርሶ አደሮቹና ኢንተርፕራይዞቹ ባለፉት ዓመታት በተሰማሩበት የሥራ መስክ ውጤታማ ከመሆን ባሻገር በነፍስ ወከፍ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ለማስመዝገብ እንደቻሉም ተናግረዋል። ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩት አርሶ አደሮች ወደ ሥራ ሲገቡ ከ14 ሺህ 400 ለሚበልጡ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ እድል ይፈጥራሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም አመልክተዋል። ወደ ኢንቨስትመንት ለተሸጋገሩ አርሶ አደሮች ከ1 ሺህ 202 ሄክታር የሚበልጥ የኢንቨስትመንት ማበረታቻ የተሰጣቸው መሆኑን ነው ኃላፊው የተናገሩት። ለአርሶ አደሮቹና ማህበራቱ በተሰማሩበት ዘርፍ ውጤታማ እንዲሆኑ የመሬት አቅርቦትና ሌሎች ማበረታቻዎች እንደተደረገላቸው የገለጹት ደግሞ የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም ኃይሌ ናቸው።   ባለፉት ዓመታት በግብርናው ዘርፍ ባከናወኑት ውጤታማ ሥራ ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩት ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች የግብርናው መስክ ሽግግር አዎንታዊ ማሳያዎች መሆናቸውን አክለዋል። በዞኑ በተያዘው በጀት ዓመት የዛሬዎቹን ጨምሮ ከ437 የሚበልጡ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮችና ማህበራት ባስመዘገቡት ከ1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ካፒታል ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸው ተመልክቷል።
በክልሉ በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት የህዝብን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ናቸው
Feb 12, 2026 79
ሐረር፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት የህዝብን ተጠቃሚነት በተጨባጭ ያረጋገጡ መሆናቸውን የክልሉ ምክር ቤት አባላት ገለጹ። ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመጠቀም ቀጣይነት ያለው ልማት ማረጋገጥ እንደሚገባም ጠቁመዋል። እየተካሄደ የሚገኘው የሐረሪ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ አመት 9ኛ መደበኛ ጉባኤ የአስፈፃሚውንና የማዘጋጃ ቤት አገልግሎት የግማሽ በጀት አመት የስራ አፈፃፀም ሪፖርት ላይ ተወያይቷል። የምክር ቤቱ አባላት በወቅቱ እንዳሉት፤ በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት የህዝብን ተጠቃሚነት በተጨባጭ ያረጋገጡ ናቸው።   የክልሉን ሁለንተናዊ ዕድገት እና የህዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራትም የበለጠ ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በተከናወኑ ተግባራት በማሕበራዊና በምጣኔ ሃብት ዘርፎች እንዲሁም በኮሪደር ልማት ውጤቶች መምጣታቸውን ገልጸዋል። የክልሉ ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ ለመሰብሰብ ቅንጅታዊ አሰራርነ ማጠናከርና ዘላቂነት ያለው ልማት ማረጋገጥ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።   የክልሉ ርዕሰ-መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በክልሉ ባለፉት ስድስት ወራት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች መሰራታቸውን አንስተዋል። በ2018 በጀት ዓመት ስድስት ወራት 3 ቢሊየን 815 ሚሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡን አንስተው የተገኘው ገቢ ከአምና ተመሳሳይ ወቅት አንፃር በ29 በመቶ ብልጫ አለው ብለዋል። ነገር ግን በግማሽ በጀት አመቱ ለመሰብሰብ ከታቀደው እና የክልሉ ኢኮኖሚ ከሚያመነጨው ሀብት አንፃር የሚፈለገውን ገቢ የመሰብሰቡ ስራ ትኩረት እንደሚጠይቅ ገልፀዋል። በክልሉ ቀጣይነት ያለው የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጠና ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጣ ለመሰብሰብ በትኩረት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። የሐረሪ ክልል ምክር ቤት ጉባኤ በክልሉ ርዕሰ-መስተዳደር ኦርዲን በድሪ የቀረበውን ሪፖርት በሙሉ ድምፅ ያፀደቀ ሲሆን በአሁን ሰአት በተለያዩ ረቂቅ አዋጆች ላይ እየተወያየ ይገኛል። ምክር ቤቱ በመደበኛ ጉባኤው ከ743 ሚሊዮን ብር በላይ ተጨማሪ በጀት ያጸደቀ ሲሆን ተጨማሪ በጀቱ ለመደበኛና ለካፒታል ፕሮጀክቶች ማስፈፀሚያ እንደሚውልም ተመላክቷል። ጉባዔው በተጨማሪም በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ በማሳለፍ ተጠናቋል።
የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
Feb 12, 2026 54
ወራቤ ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦ በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ። በስልጤ ዞን የተገነባው የሚቶ ኤድነባ መስኖ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማእረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ሃላፊ መሃመድ ኑርዬ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት፤ በክልሉ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው።   የውሃ አማራጮችን በመጠቀም የመስኖ ልማት በመተግበር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማጎልበት መቻሉን ጠቁመዋል። ዛሬ ወደ ስራ የገባው የሚቶ ኤድነባ መስኖ ፕሮጀክት የዚሁ አካል መሆኑን አንስተዋል። ከፍተኛ ወጪ ወጥቶባቸው የተገነቡ የመስኖ ፕሮጀክቶች ደህንነታቸው ተጠብቆ እንዲቆይ ህብረተሰቡ በተገቢው መንገድ መጠቀም እንደሚገባው አስገንዝበዋል። የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖ ተቋማት ልማትና አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር ካሳዬ ተክሌ፤በተያዘው በጀት አመት በክልሉ 12 የመስኖ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን ተናግረዋል።   የሚቶ ኤደነባ የመስኖ ፕሮጀክትም በተያዘለት 6 ወራት ጊዜ ውስጥ ግንባታው ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ለአገልግሎት መብቃቱን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ 54 ሄክታር ማሳ እንደሚያለማና 200 አባወራ እና እማወራዎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ጠቁመዋል። የከርሰ ምድር ውሀን በፀሃይ ሃይል በመሳብ ለመስኖ አገልግሎት እንዲውል የሚያደርገው ፕሮጀክቱ ከ105 ሚሊዮን ብር ወጪ እንደተደረገበትም ገልጸዋል። የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘይኔ ቢልካ፤ አርሶ አደሮች ይህን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም በዘመናዊ መንገድ አልምተው የቤት ውስጥ ፍጆታን በማሟላት ለውጪ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶች ላይ በማተኮር ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።   የመስኖ ፕሮጀክቱን ከሚጠቀሙ አርሶ አደሮች መካከል አቶ አብድልሰላም ሃሰን ከሁለት ሄክታር በላይ መሬት ላይ አትክልትና ፍራፍሬ ማልማታቸውን ተናግረዋል። ሌላው አርሶ አደር ሃጅ ዋበላ ተማም በአራት ሄክታር መሬታቸው ላይ ሰብል እና አትክልት ማምረት መጀመራቸውን ገልጸው የመስኖ ፕሮጀክቱን በአግባቡ በመያዝ አገልግሎት እንዲሰጥ በተገቢው መንገድ እንደሚጠቀሙ ተናግረዋል።   በእለቱም የወራቤ ከተማ አስተዳደር ውስጥ እየተከናወነ ያለው የ1 ነጥብ 6 ኪ.ሜ እንዲሁም ከሚቶ -ባራ- ቡልቡላ ድረስ እየተገነባ ያለው የ38 ኪሎ ሜትር የኮንክሪት አስፋልት መንገድ ግንባታ ያለበት ሁኔታ እንዲሁም የወራቤ ከተማ የወንዝ ዳርቻ ልማት ጉብኝት ተደርጓል። በስነስርዓቱ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የስልጤ ዞን የስራ ሃላፊዎች እና የአካባቢው ማህበረሰብ ተወካዮች ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያ በግብርና ትራንስፎርሜሽን ያስመዘገበችው ስኬት ለሌሎች ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው
Feb 12, 2026 90
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በግብርና ትራንስፎርሜሽንና በምርታማነት ያስመዘገበችው ውጤት ለሌሎች አፍሪካውያን ትልቅ ምሳሌ መሆኑን በአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ ገለጹ። 39ኛው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባኤ "ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት" በሚል መሪ ሀሳብ በመጪው ቅዳሜና እሁድ በአዲስ አበባ ይካሄዳል። ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ አካታች የአፍሪካ ግብርና ልማት ፕሮግራም (CAADP) እና የዲጂታል ግብርና አስፈላጊነት ላይ መግለጫ ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ የምግብ አመራረት ስርዓቷን ለማጠናከር የጀመረችው አስደናቂ የግብርና ልማት ጉዞ በተለይ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለሌሎችም ምሳሌ መሆኑን ገልጸዋል። ሀገሪቱ ወደ ዘመናዊ ግብርና እየተሸጋገረች ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፥ በዚህም ትልቅ የታሪክ ምዕራፍ ላይ እንደምትገኝ ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ከየት እንደጀመረች እና አሁን ያለችበትን ደረጃ ተገንዝበናል፤ አሁን ስንዴ ወደ ውጭ በመላክ ላይ ትገኛለች ይህ ትልቅ ስኬት ነው፣ እኛም ይህንን እናደንቃለን ብለዋል። የኢትዮጵያ ብዝኃ የልማት አጀንዳዎች እንዳሏት በማውሳት፥ ግብርናን ማዘመን ላይም ፈጠራ፣ የፖሊሲ አቅጣጫና የፖለቲካ ቁርጠኝነት ሲቀናጅ የሚያመጣውን ውጤት ለዓለም አሳይታለች ነው ያሉት። ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በምግብ ምርቶች ላይ ያላቸውን የውጭ ጥገኝነት ለመቀነስ የኢትዮጵያን ተሞክሮ እንዲከተሉ አስገንዝበዋል። የአፍሪካን ግብርና ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር በዘርፉ የዲጂታል ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማስፋት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ኮሚሽነሩ፣ ህብረቱ በዚህ ላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ የዲጂታል ግብርና ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ለአህጉሪቱ አብነት መሆኑን ጠቅሰው ሌሎች አባል ሀገራትም የግብርና ልማትን ማዘመን ቀዳሚ ሥራቸው ሊሆን ይገባል ብለዋል። እ.አ.አ እስከ 2030 በሚተገበረው የአፍሪካ የዲጂታል ግብርና ስትራቴጂ አማካኝነት በግብርና እሴት ሰንሰለቶች ውስጥ ዲጂታል መሳሪያዎችን ለመተግበር አህጉራዊ ማዕቀፍ እየተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል። በቴክኖሎጂ የተደገፉ የዲጂታል የምክር አገልግሎቶች፣ የአየር ንብረት መረጃ ስርዓቶችና የዲጂታል ገበያ ቦታዎች ለዘርፉ ዕድገት ጉልህ ሚና እንዳላቸው ጠቅሰዋል። ይህም የምግብና ስርዓተ ምግብ ደህንነትን ከማረጋገጥ ባለፈ በተለይ ለወጣቶች ሰፊ የኢኮኖሚ ዕድሎችን እንደሚፈጥር ነው ያነሱት። እንደ ኮሚሽነሩ ማብራሪያ የመጀመሪያው የአፍሪካ ህብረት ዲጂታል ግብርና ኮንፍረንስ ከተካሄደ በኋላ፣ የአፍሪካ ህብረት በዘርፉ ዲጂታል ፈጠራን ተቋማዊ ለማድረግ በከፍተኛ ቁርጠኝነት እየሰራ ይገኛል።
በአምራች ኢንዱስትሪው እየታየ ያለው መነቃቃት መንግስት ለዘርፉ የሰጠው ድጋፍና ክትትል ውጤት ነው
Feb 12, 2026 77
ደብረ ብርሃን ፤ የካቲት 5/2018(ኢዜአ)፦ በአምራች ኢንዱስትሪው እየታየ ያለው መነቃቃት መንግስት ለዘርፉ የሰጠው ድጋፍና ክትትል ውጤት መሆኑን በምክትል ርእሰ መሥተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አሥተባባሪ አህመዲን መሐመድ(ዶ/ር) ገለጹ። በደብረ ብርሃን ከተማ በአንድ ቢሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ አራት አምራች ኢንዱስትሪዎች ተመርቀው ወደ ምርት ገብተዋል።   በምክትል ርእሰ መሥተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አሥተባባሪ አህመዲን መሐመድ(ዶ/ር) በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደገለጹት፣ መንግስት ልዩ ትኩረት ከሰጣቸው የኢኮኖሚ ዘርፎች አንዱ ኢንዱስትሪ ነው።   በዘርፉ ያጋጥሙ የነበሩ ችግሮችን በመለየትና መፍትኤ በመስጠትም አሁን ላይ ተጨባጭ ውጤት መምጣቱንም ገልጸዋል። በተለይም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኢንዱስትሪው መነቃቃት ትልቅ ዕድል መፍጠሩንም አንስተዋል። ቀደም ባሉት ጊዜያት የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ከ46 በመቶ ያልበለጠ የነበረ ሲሆን አሁን ላይ ለዘርፉ በተሰጠው ትኩረት 64 በመቶ መድረሱን አመልክተዋል። በተያዘው በጀት ዓመት ስድስት ወራት ብቻም 93 በጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጅተው ወደ ስራ የገቡ አንቀሳቃሾች ወደ መካከለኛ የአምራች ኢንዱስትሪ መሸጋገራቸውን ተናግረዋል። መንግስት ለአምራች ኢንዱስትሪ በሰጠው ድጋፍና ክትትል በዘርፉ መነቃቃት መፍጠሩንም ተናግረዋል።   የአማራ ክልል ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ሃላፊ እንድሪስ አብዱ በበኩላቸው፣ በክልሉ ሰላምን ከማረጋገጥ ጎን ለጎን ለኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መስፋፋት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ሰባት ወራት ብቻ በአማራ ክልል 85 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት መሸጋገራቸው ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለተኪ ምርት ዕድገት ቁልፍ ሚና ተጫውቷል ብለዋል። የደብረ-ብርሃን ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ በድሉ ውብሸት፣ ከተማዋ ምቹ የኢንዱስትሪ መዳረሻ እንደመሆኗ በዘርፉ ለመሰማራት የሚፈልጉ ባለሀብቶች ቁጥር እያደገ ነው ብለዋል።   ለዚህ ደግሞ በአንድ ቢሊዮን ብር ወጪ ተገንብተው ወደ ሥራ የገቡ የዱቄት፣ የፕላስቲክና የጫማ ማምረቻ አራት ኢንዱስትሪዎች ማሳያ ናቸው ብለዋል። በከተማዋ በበጀት ዓመቱ እስካሁን ድረስ 15 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት መሸጋገራቸውን ጠቁመው፣ በዚህም ከ7ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን አመልክተዋል።
የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ የተመዘገቡ ስኬቶችን ለማስቀጠል የሚያደርገውን ትብብር አጠናክሮ ይቀጥላል
Feb 12, 2026 83
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ የተመዘገቡ ስኬቶችን ለማስቀጠል የሚያደርገውን ትብብር አጠናክሮ እንደሚቀጥል የባንኩ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አና ቤርዴ ገለጹ፡፡ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሺዴ ከዓለም ባንክ ከማኔጂንግ ዳይሬክተሯ እና ከባንኩ የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ቀጣና ምክትል ፕሬዚዳንት ንዲያሜ ዲዮፕ ጋር ተወያይተዋል፡፡   በውይይታቸው በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶችን ጨምሮ ለዘላቂና አካታች ልማት እንዲሁም የተረጋጋ የማክሮ ኢኮኖሚን ለማረጋገጥ ቅድሚያ በሚሰጣቸው ጉዳዮች ዙሪያ መምከራቸው ተገልጿል፡፡ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሺዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ኢትዮጵያ በግሉ ዘርፍ የሚመራ ኢኮኖሚን ለመገንባት የምታደርገውን ሽግግር ለማፋጠን የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ ይገኛሉ፡፡ በዚህም የግሉን ዘርፍ የልማት እድሎች ለማስፋትና የኢኮኖሚ ማሻሻያውን ትግበራ ለማጠናከር የዓለም ባንክ ቀጣይነት ያለው ትብብር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡   የዓለም ባንክ ማኔጂንግ ዳይሬክተሯ አና ቤርዴ በበኩላቸው በገንዘብ ፖሊሲ አስተዳደር፣ የዋጋ ንረት ጫናን በመቀነስ፣ የውጭ ምንዛሪ ክምችትን በማሳደግ እንዲሁም የውጭ ምንዛሪ ገበያን በማጠናከር ረገድ የተከናወኑ ተግባራትን አድንቀዋል፡፡ ባንኩ በኢትዮጵያ የግሉን ዘርፍና የአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን አቅም በማሳደግ ለኢኮኖሚ ማሻሻያውና ቅድሚያ የሚሰጣቸውን የረዥም ጊዜ የልማት ዘርፎች ውጤታማነት ለማረጋገጥ ድጋፉን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ ሁለቱ ወገኖች በስራ እድል ፈጠራ፣ በኢነርጂ ልማት፣ በሎጂስቲክስ፣ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን፣ በግብርና፣ በግሉ ዘርፍ፣ በአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ልማትና የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን ለመቋቋም ትብብራቸውን ለማጠናከር ተስማምተዋል፡፡ በተጨማሪም በማሻሻያው የተገኙ ውጤቶችን ለማስቀጠል የተቋማትን አቅም ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት በመስጠት፤ አካታች ልማትና ዘላቂ የኢኮኖሚ እድገትን ለማረጋገጥ ቁርጠኛ መሆናቸውን አመልክተዋል፡፡
የቡና ጥራትን በማስጠበቅ ከዘርፉ የሚገኘውን የውጭ ምንዛሪ የማሳደግ ስራ እየተከናወነ ነው
Feb 12, 2026 70
ጊምቢ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፡-የቡና ጥራትን በማስጠበቅና ግብይትን በማሳለጥ ከዘርፉ የሚገኘውን የውጭ ምንዛሪ ለማሳደግ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን አስታወቀ። የተለያዩ ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት የቡና ፈስቲቫል በጊምቢ ከተማ የተካሄደ ሲሆን ባለሥልጣኑ የቡና ጣእምና ጥራት ማረጋገጫ ማዕከልንም ዛሬ በይፋ ስራ አስጀምሯል።   በፌስቲቫሉ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን መሠረታዊ አገልግሎት ስራ አስፈፃሚ አቶ ብርሃኑ ቆርቾ እንዳሉት፤ የቡና ጥራትን በማስጠበቅና የግብይት ሰንሰለቱን በማሳለጥ የቡና አምራቹን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው። ለዚህም በቡና አምራች አካባቢዎች የቡና ጥራትና የጣእም ደረጃ የሚያረጋግጡ ማዕከላት በቅርበት እየተከፈቱ መሆኑን ጠቁመው ይህም ቡና አምራቹ አርሶ አደርና በዘርፉ የተሰማሩ ነጋዴዎች ለጥራት ትኩረት እንዲሰጡ ያነሳሳል ብለዋል። የቡና ጥራትን በዘላቂነት ለማስጠበቅ መንግስት የተለያዩ ድጋፎች ሲያደርግ መቆየቱን ገልጸዋል። እንዲሁም አርሶ አደሮች ጥራቱን የጠበቀ የቡና ምርት እንዲሰበስቡም ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ስልጠና መሰጠቱን ተናግረዋል። ይህም የቡና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ሀገራችን ከዘርፉ የምታገኘውን የውጭ ምንዛሪ እያሳደገው እንደሚገኝ አስታውቀዋል። የምእራብ ወለጋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ተሊላ ተረፈ በበኩላቸው፤ በዞኑ ቡናን በብዛትና በጥራት በማምረት ለማዕከላዊ ገበያ የማቅረብ ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ዛሬ የቡና ጣእምና ጥራት ማረጋገጫ ማዕከል ወደ ስራ መግባቱም ይህንን ስራ ለማጠናከር እና የዞኑ ቡና አምራች አርሶ አደርን የረጅም አመታት ጥያቄ የሚፈታ መሆኑን ገልጸዋል። የዞኑን የቡና ምርት ጥራት ደረጃን ለማሻሻልም ቡና አምራች አርሶ አደሮች፣ ነጋዴዎች፣ አመራሮች እና ባለሙያዎችን ያሳተፈ ውይይት መካሄዱን ገልጸዋል።
በበጀት ዓመቱ ያለፉት ስድስት ወራት በዋና ዋና የልማት ዘርፎች የተሻለ ውጤት ተመዝግቧል - ርዕሰ መስተዳድር ኢ/ር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)
Feb 12, 2026 52
ታርጫ፣የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በበጀት ዓመቱ ያለፉት ስድስት ወራት በዋና ዋና የልማት ዘርፎች የተሻለ ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ። የምክር ቤቱ 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 9ኛ መደበኛ ጉባኤ በታርጫ ከተማ እየተካሄደ ነው። ርዕሰ መስተዳድሩ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት የስድስት ወራት የስራ አፈፃፀም ሪፖርት በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራት በተሰራው ስራ በዋና ዋና የልማት ዘርፎች የተሻለ ውጤት መመዝገቡን ገልፀዋል። በበጀት ዓመቱ አጋማሽ በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ጸጋዎችንና የልማት ሀይሎችን በመጠቀም በልማት፣ በሰላምና በመልካም አስተዳደር ዘርፎች ፈጣንና ቀጣይነት ያለው ሁለንትናዊ እድገት እንዲመዘገብ ሰፊ ርብርብ ተደርጓል ብለዋል። በግብርናው ዘርፍ በበ2017/18 ምርት ዘመን ባለፉት ስድስት ወራት 384 ሺህ 160 ሄክታር መሬት በማልማት 20 ሚሊዮን 390 ሺህ 755 ኩንታል ምርት መሰብሰብ መቻሉን ለአብነት አንስተዋል። በአጠቃላይ የግብርናው ዘርፍ ያለውን አቅም ለመጠቀም በሚደረገው ጥረት አበረታች ውጤቶች እየተመዘገቡ እንዳሉ ጠቅሰው ምርትና ምርታማነትም እያደገ ይገኛል ብለዋል። በዚህም ከቤት ፍጆታ ባለፈ ገበያን የሚያረጋጋ ምርት እየተገኘ መሆኑን ጠቁመው ዘርፉን ለማጠናከር የግብርና ግብዓቶችና ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ የማድረግ ስራ በቅንጅት መሰራቱንም አመልክተዋል። በሌማት ትሩፋት በዶሮ፣ በወተት፣ በዓሳና በማር መንደሮችን ከማደራጀት ባለፈ የእንቁላል፣ የስጋና የወተት ምርታማነትን ለማሳደግ የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ባለፉት ስድስት ወራት በመደበኛና ሰው ሰራሽ፣ በተሻሻሉ ኮርማዎች፣ በሲንክሮናይዜሽን ከ30 ሺህ በላይ ላሞችንና ጊደሮችን ማግኘት የተቻለ ሲሆን 2 ሚሊዮን 67 ሺህ 649 የአንድ ቀን ጫጩቶች፣ ቄብና ኮክኔዎችን ማሰራጨት ተችሏል ብለዋል። በሌላ በኩልም ክልሉን የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ እየተሰራ ሲሆን ባለፉት ስድስት ወራት በአገልግሎት፣ በግብርናና በኢንዱስትሪ ዘርፎች ለ57 ባለሀብቶች ፍቃድ መሰጠቱንም በሪፖርታቸው አንስዋል። ከመደበኛና ማዘጋጃ ቤታዊ ገቢ በበጀት ዓመቱ ከ18 ቢሊዮን 420 ሚሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ ታቅዶ ባለፉት ስድስት ወራት በተደረገው ሰፊ ርብርብ ከ8 ቢሊዮን 358 ሚሊዮን 681 ብር በላይ መሠብሰብ መቻሉን አብራርተዋል። ገቢው ከተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከ84 በመቶ በላይ ብልጫ እንዳለውም አመልክተዋል። የምክር ቤቱ ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ ወንድሙ ኩርታ በበኩላቸው በየደረጃው በሚገኙ ቋሚ ኮሚቴዎች በተደረገ የአስፈፃሚ አካላት ክትትልና ግምገማ የተሻለ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። በተለይም የህዝብ ተጠቃሚነትን የሚያሻሽሉ ተግባራት አፈጻጸም ክትትል ውጤት ማምጣቱን ጠቅሰው ምክር ቤቱ የሚያደርገውን የክትትልና ድጋፍ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል። ምክር ቤቱ በሁለት ቀናት ቆይታው፣ የአስፈፃሚ አካላት የስድስት ወራት ሪፖርት በመገምገምና የተለያዩ ሹመቶችንና አዋጆችን በማፅደቅ በሌሎች አጀንዳዎች ላይ እንደሚመክርም ይጠበቃል።
በክልሉ የተቀናጀ የግብርና አሰራር ስርዓትን በመተግበር የህዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል
Feb 12, 2026 64
ወልቂጤ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ):- በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተቀናጀ የግብርና አሰራር ስርዓትን በመተግበር የህዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉ ተመላከተ። በክልሉ ጉራጌ ዞን በምግብ እና በሃድያ ዞን በእንስሳት ሀብት ልማት ማጠናከሪያ ፕሮግራም እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ላይ የመስክ ምልከታ ተካሄዷል፡፡   የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የተሰሩ የመስኖ ልማት፣ በክላስተር የለማ የቡና ማሳና የቡና ችግኝ ጣቢያ ላይ ምልከታ የተደረገ ሲሆን በጎታም ወንዝ ላይ የተገነባው ድልድይም ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ተወካይ አቶ አህመድ ሀቢብ በወቅቱ እንዳሉት በክልሉ እየተተገበሩ ያሉ የግብርና ኢኒሼቲቮች የአርሶ አደሩን ህይወት እየቀየሩ መሆኑን ተናግረዋል።   በግብርናው ዘርፍ አዳዲስ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ ለወጣቶች የስራ እድል ለመፍጠር፣ ለኢንዱስትሪ በቂ ምርት ለማቅረብና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን ለመተካት የሚያስችል ዕድል እየተፈጠረ ነው ብለዋል። ከዚህም ባለፈ ዝርያቸው የተሻሻሉ እና ምርታማ የሆኑ የቡና ችግኞችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ ተጨማሪ ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን ማጎልበት እየተቻለ መሆኑን ጠቁመዋል። በግብርና ሚኒስቴር የስርዓተ ምግብ ማጠናከሪያ ፕሮግራም ብሔራዊ አስተባባሪ አቶ ከበሩ በላይ በበኩላቸው በምርምር፣ በውሃ እና መስኖ፣ በቴክኖሎጂ፣ በግብዓት አቅርቦት፣ በገበያ መሰረተ ልማት ግንባታና ትስስር ስኬታማ ስራዎች ተመዝግበዋል ብለዋል።   የአርሶ አደሩ ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር በማድረግ በምግብ ራሱን እንዲችል ከማድረግ ባለፈ ያመረተውን ምርት ወደ ገበያ በማውጣት ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኝ የማድረግ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል። የስርዓተ ምግብ ማጠናከሪያ ፕሮግራሙ በክልሉ በአራት ዞኖች በሚገኙ አስር ወረዳዎች ከ78 በላይ በሚሆኑ ፕሮጀክቶች በስኬት እየተከናወነ መሆኑንም አንስተዋል። በክልሉ የቸሀ ወረዳ ነዋሪው አቶ ጀማል ባድሳዊ መንግስት ጥምር ግብርና ላይ እንዲያተኩሩ በማድረግ ምርትና ምርታማነታቸውን በማሳደግ ህይወታቸው መቀየሩን ተናግረዋል ። ክፍት የተደረገው የጎታም ድልድይ ለአካባቢው ማህበረሰብ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ጠቅሰው ያመረቱትን ምርት ወደ ገበያ ለማውጣት እና የግብርና ግብዓትን በወቅቱ ለማግኘት እንደሚያስችላቸውም ተናግረዋል። በቀረበላቸው የሶላር ቴክኖሎጂ ተጠቅመው ከወንዝ ውሃ በመጥለፍ በማህበር ተደራጅተው አትክልትና ፍራፍሬ በማምረት ለገበያ እያቀረቡ መሆናቸውን የተናገረችው ደግሞ ወይዘሪት አምሪያ ሙንታቃ ናት።   በመስክ ምልከታው መርሐ ግብር ላይ የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞን እና የወረዳ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና የህብረተሰብ ክፍሎች እና የአለም ባንክ የፕሮጀክቱ አስተባባሪዎች ተገኝተዋል።  
የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በምግብ ራስን ከማስቻል ባለፈ ከተረጂነት ለመውጣት እገዛ እያደረገ ነው
Feb 12, 2026 75
አርባምንጭ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ) :- በጋሞ ዞን የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በምግብ ራስን ከማስቻል ባለፈ ከተረጂነት ለመውጣት እገዛ እያደረገ መሆኑ ተገለጸ። በዞኑ ከ1 ሺህ 300 ሄክታር በላይ የበጋ ስንዴ በአርሶ አደሮችና በባለሀብቶች ማሳ እየለማ የሚገኝ ሲሆን የሚጠበቀውን ምርት ለማግኘት የሚያስችል የተባይ ቁጥጥርና እንክብካቤ እየተደረገ እንደሚገኝም ተመልክቷል። የበጋ ስንዴ ልማት ከተጀመረ ወዲህ ከተረጂነት ወጥተን በምግብ ራሳችንን ለመቻል እየተደረገ ባለው ጥረት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ያሉት ደግሞ በቁጫ ወረዳ ፋንጎ ቀበሌ አርሶ አደር ሚሊዮን በየነ ናቸው። ከበጋ ስንዴ በሚገኝ ጥቅም ልጆቻችንን ለማስተማርና ኑሮአችን ለመለወጥ ብሎም ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ሳንቸገር እንድንከውን አቅም ሆኖናል ብለዋል። በሁለት ሄክታር መሬት ላይ ስንዴን በመስኖ እያለሙ መሆናቸውን ጠቅሰው የእንክብካቤና የቁጥጥር ስራ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። የግብርና ባለሙያዎች ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እያደረጉ መሆኑን ገልጸው በቴክኖሎጂ በመታገዝ ከአንድ ሄክታር ከ40 ኩንታል በላይ ለማግኘት ማቀዳቸውን ተናግረዋል። በጋሞ ዞን በምዕራብ አባያ ወረዳ አልጌ ቀበሌ በ20 ሄክታር መሬት ላይ ስንዴ እያለማ የሚገኘው ሳውዝ አግሮ ኢንዱስትሪ ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ ብሩክ ማማ ምርቱ በጥሩ ቁመና ላይ መሆኑን ገልጸዋል። ወረዳው የምርጥ ዘር እና የማዳበሪያ እንዲሁም የሙያ ድጋፍ ማድረጉን ጠቅሰው የስንዴ ምርቱ በምግብ ራስን የመቻል ዕድልን የማስፋት አማራጭ እንደሚሰጥም አስረድተዋል። ድርጅቱ ከዛሬ 5 ዓመት ጀምሮ ስንዴን በመስኖ በስፋት በማምረት ለአካባቢው መነቃቃት የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ጠቅሰው ከዘንድሮው ምርትም ከአንድ ሄክታር 45 ኩንታል ለማግኘት አቅደን እየሠራን እንገኛለን ብለዋል። የአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ግብርና ባለሙያ አቶ ሳሙኤል ኤርቦ በበኩላቸው የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ቴክኖሎጂን በአግባቡ እንዲጠቀም ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ስራ የአርሶ አደሩን የግብርና ባህል በመቀየር ጥሪት እንዲያፈሩና ኑሮአቸውን እንዲያሻሽሉ እገዛ እያደረገ መሆኑን አመልክተዋል። የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ሃላፊ አቶ ወርቅነህ ካልሳ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት የበጋ መስኖ ስንዴ በምግብ ራስን የመቻል ራዕይን በተጨባጭ እያሳካው ይገኛል ብለዋል። በተለይ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት አርሶ አደሮች ከተረጂነት ወጥተው የምግብ ሉዓላዊነታቸውን እንዲያረጋግጡ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ በተያዘው በጋ ወቅት 1 ሺህ 380 ሄክታር መሬት ስንዴ በመስኖ እየለማ እንደሚገኝ አመልክተው ከዚህም ከ46 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት የሚጠበቅ መሆኑን ገልጸዋል።
በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ ከ102 ሺህ በላይ ቱሪስቶች ሐረሪ ክልልን ጎበኙ
Feb 12, 2026 83
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፡- በ2018 የበጀት ዓመት የመጀመሪያ አጋማሽ ከ102 ሺህ 382 በላይ የውጭና የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች ሐረሪ ክልልን መጎብኘታቸውን የክልሉ ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለፁ። የሐረሪ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት 9ኛ መደበኛ ጉባዔ እየተካሄደ ይገኛል። በጉባዔው ላይ የክልሉ መንግሥት በ2018 የግማሽ ዓመት ያከናወናቸውን ሥራዎች ሪፖርት ያቀረቡት ርዕሰ መሥተዳድር ኦርዲን፤ በቱሪዝም ዘርፍ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል። የቱሪስት መዳረሻ ልማት ሥራዎች፣ የሐረር ዓለም አቀፍ ዕውቅና እንዲሁም እየተከናወኑ ያሉ የማስተዋወቅ ሥራዎች ለከተማው ተጨማሪ ዐቅም ከመፍጠር ባሻገር የቱሪስት ፍሰቱ ብሎም የቆይታ ጊዜ እንዲጨምር ማስቻሉንም አብራርተዋል። በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ ክልሉን ከጎበኙ ቱሪስቶችም ከ226 ሚሊየን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ጠቁመዋል። በአራተኛው ዙር የጀጎል የውስጥ ለውስጥ መንገዶች መልሶ ማልማት ፕሮግራምም፤ በመንግሥታዊ የክልሉ ተቋማት፣ ወረዳዎችና የግል ባለሃብቶች ተሳትፎና ከዘጠኝ ኪሎ ሜትር በላይ የኮሪደር ልማት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። በሌላ በኩል ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል። የመስኖ ልማት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብሮችን በማስፋት፣ የሜካናይዜሽን አጠቃቀምና የምርጥ ዘር አቅርቦትን በማሳደግ የግብርና ዘርፍ ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት መሠራቱንም አንስተዋል። በዚህም በብርዕና አገዳ ሰብሎች 9 ሺህ 374 ኩንታል በማልማት 150 ሺህ 572 ኩንታል ምርት ማምረት መቻሉን አስታውቀዋል። የጥራጥሬ ሰብል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሠራው ሥራም 2 ሺህ 295 ኩንታል ቦሎቄ፣ 26 ሺህ 55 ኩንታል የለውዝ እንዲሁም 156 ሺህ 740 ኩንታል የፍራፍሬ ምርት መሰብሰብ ተችሏል ነው ያሉት። እንዲሁም በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር በተሠሩ ሥራዎችም 10 የወተት፣ ሁለት የእንቁላል፣ አራት የዓሣ እና ሁለት የማር መንደሮችን መፍጠር መቻሉን በሪፖርቱ አቅርበዋል። በዚህም 15 ነጥብ 2 ሚሊየን ሊትር ወተት፣ ዘጠኝ ሚሊየን 288 ሺህ እንቁላል፣ 774 ነጥብ 22 ቶን የሥጋ፣ 19 ነጥብ 37 ቶን የማር ምርት ማምረት መቻሉን አክለዋል። በበጋ መስኖ የአትክልትና የሥራሥር ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በተሠራው ሥራም በሁለት ዙር 2 ሺህ 842 ሔክታር ማልማት ተችሏል ብለዋል። የሰብል ግብዓት አቅርቦትና አጠቃቀምን ለማሻሻልም 3 ሺህ 931 ኩንታል ሰው ሠራሽ ማዳበሪያ፣ 35 ሺህ 658 ሜትር ኪዩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ኮምፖስት ማቅረብ መቻሉን አመላክተዋል። በክልሉ የዶሮ ብዜትና ስርጭት ማዕከል 40 ሺህ 500 የዶሮ ጫጩቶችን ማቅረብ መቻሉን ገልጸው፤ የዓሣ ጫጩት ስርጭትን በተመለከተም 28 ሺህ 500 ጫጬቶችን ማሰራጨት መቻሉን ጠቁመዋል። የገጠር ምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በተሠራው ሥራም በቋሚ ቀጥተኛ ድጋፍ 9 ሚሊየን 210 ሺህ 740 ብር ድጋፍ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የኅብረት ሥራ ማኅበራትን በተመለከተም 841 አባላትን ያቀፉ 13 ማኅበራት መደራጀታቸውን ርዕሰ መሥተዳድሩ በሪፖርቱ አመላክተዋል።
ኢትዮጵያ ሁሌም አዳዲስ ነገሮችን በማሳየት ያለፈው ብቻ ሳይሆን የመጻዒው ፓን አፍሪካኒዝም አርዓያነቷን አጠናክራ ቀጥላለች
Feb 12, 2026 88
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ በየዓመቱ በሚካሄደው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባኤ ሁሌም አዳዲስ ነገሮችን በማሳየት ያለፈው ብቻ ሳይሆን የመጻዒው ፓን አፍሪካኒዝም አርዓያነቷን አጠናክራ ቀጥላለች ሲል የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ። አገልግሎቱ በአዲስ አበባ የሚካሄደውን 39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤና የአፍሪካ ጣልያን ጉባኤን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል። ኢትዮጵያ በየዓመቱ በሚካሄደው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባኤ ሁሌም አዳዲስ ነገሮችን በማሳየት ያለፈው ብቻ ሳይሆን የመጻዒው ፓን አፍሪካኒዝም አርዓያነቷን አጠናክራ ቀጥላለች ብሏል። የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል፦ ኢትዮጵያ የአህጉራዊ አንድነትና የፓን-አፍሪካኒዝም ማሳያ የሆነውን 39ኛውን የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባኤን እንዲሁም ጎን ለጎን የሚካሄደውን የታሪካዊውን የአፍሪካ-ጣሊያን ጉባኤን በድምቀት ለማስተናገድ ዝግጅቷን አጠናቃለች። ከየካቲት 6 እስከ 8 ባሉት ቀናት ሃገራችን ሁለት ዐበይት ጉባዔዎችን ታስተናግዳለች። የመጀመሪያው የካቲት 6 ቀን 2018 ዓ.ም የሚካሄደው የአፍሪካ-ጣሊያን ጉባኤ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ለ39ኛ ጊዜ የሚካሄደው የአፍሪካ መሪዎች ጉባኤ ነው። የዘንድሮው የአፍሪካ ኅብረት የመሪዎች ጉባኤ፣ “የ2063 የአጀንዳ ግቦችን ለማሳካት ዘላቂ የውሃ አቅርቦት እና ደህንነቱ የተጠበቀ የንፅህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ” በሚል መሪ ቃል ይካሄዳል።ይህ ርዕሰ ጉዳይ የአፍሪካን ለዘላቂ ልማት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያንፀባርቅ ሲሆን፣ የ2063 አጀንዳን ከግብ ለማድረስ የረጅም ጊዜ ራዕይን በመሰነቅ እየገሰገሰች መሆኗን የሚያመላክት ነው። ከዚህ አንጻር ሃገራችን ለአፍሪካውያን ልታቀርባቸው የምትችላቸው በርካታ ተሞክሮዎች አላት። ሃገራችን ኢትዮጵያ፦ • በአረንጓዴ አሻራ ባለፉት ሰባት ዓመታት ወደ ሃምሳ ቢሊዮን የሚገመት ችግኝ በመትከል የደን ሽፋናችንን ከ17 በመቶ ወደ 23 በመቶ ማሳደግና ለአዛላቂ ልማት ያለንን ቁርጠኝነት ማሳየት ችለናል። • ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን ጨምሮ የሃይድሮ፣ የነፋስ እና የጸሃይ ታዳሽ ሃይል አማራጮችን በመጠቀም የኢነርጂ ፍላጎቷን ከማሳደግም አልፎ ለጎረቤቶች ጭምር መትረፍ ችላለች። በተጨማሪም በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን በመከልከል ለታዳሽ ኢነርጂ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር አሳይታለች። • በከተማ የኮሪደር ልማት እና በወንዝ ዳርቻ ልማት ከተሞችን ጽዱና ውብ ማድረግ እና የአካባቢ ብክለትን የቀነሱ ደማቅ ከተሞችን የመፍጠር ጥረት በመዲናችን ጀምራ በበርካታ የሃገራችን ከተሞች እየቀጠለች ትገኛለች። • ከፕላስቲክ የጸዳ አካባቢን ለመፍጠር የአንድ ጊዜ የፕላስቲክ መያዣዎችን በመከልከል ለዘላቂ ልማትና አካባቢ ጥበቃ ያላትን ቁርጠኝነት ዳግም አስመስክራለች። • በቀጣይነትም የውሃ ሃብቷን በአግባቡና ውጤታማ በሆነ መንገድ ለመጠቀም የሚያስችሉ ሁለንተናዊ እርምጃዎችን እየወሰደች ትገኛለች። ከኅብረቱ ጉባኤ አስቀድሞ የአፍሪካ-ጣሊያን ጉባኤ የሚካሄድ ሲሆን፣ ይህም የአፍሪካ-ኢጣሊያ የትብብር ማዕቀፎችን ይበልጥ የሚያጠናክር ነው። የአፍሪካ ጣሊያን ፎረም መካሄድ ከጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ከሮም ውጭ ሲካሄድ ይህ የመጀመሪያው ሲሆን በአፍሪካ አፈር ሲካሄድ የመጀመሪያዋ መዳረሻ ኢትዮጵያ መሆኗ ሃገራችን አፍሪካን ከተቀረው ዓለም ከማስተሳሰር አንጻር ያላትን ከፍተኛ አቅም የሚያሳይ ነው። የጉባዔው ማዕከላዊ አጀንዳ እ.ኤ.አ በ2024 በሮም ይፋ የተደረገውን የማቴይ ዕቅድ አፈጻጸም መገምገም እና ቀጣይ አቅጣጫዎችን ማስቀመጥ ነው። የጉባኤው ዋና ዋና አምዶች በሆኑት ኢነርጂ፣ ግብርና፣ ትምህርትና ስልጠና፣ ጤና፣ ውሃ፣ መሰረተልማት ሃገራችን በርካታ ተሞክሮዎችን ማቅረብና አጋርነቶችን መመስረት የሚያስችላት ቁመና ላይ ትገኛለች። በእነዚህ ጉባኤዎች ርዕሰ ብሔሮች፣ ጠቅላይ ሚንስትሮች፣ ምክትሎች እና የውጭ ጉዳይ ሚንስትሮችን ጨምሮ በአጠቃላይ ከ17 ሺህ በላይ የልዑካን ቡድን አባላት ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል። እነዚህን ጉባዔዎች ለመዘገብ ከ800 በላይ የሚዲያ ባለሞያዎች ፈቃድ ጠይቀዋል። በቀጣይ ቀናት የአህጉራችን ዋና ዋና ሚዲያዎች ዐይን እና ጆሮ ሃገራችን ላይ ያነጣጥራል። ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሞቿን በሚያስጠብቁ እና ከግብ በሚያደርሱ ውይይቶች ላይ በንቃት ለመሳተፍ ተዘጋጅታለች። በዚህም የአፍሪካ የጋራ ጥቀሞችን ለማረጋገጥ የበኩሏን አስተዋጽኦ ታደርጋለች። የአፍሪካ መሪዎችና ልዑካን ቡድኖች በቆይታቸው ከዲፕሎማሲያዊ ስራዎቻቸው ባሻገር፣ የሀገራችንን የልማት ሥራዎች እና የቱሪስት መዳረሻዎች እንዲጎበኙና በቀጣይነት እየተመዘገቡ ያሉ የልማት ውጤቶቻችንን እንዲመለከቱ ሰፊ ዝግጅት ተደርጓል። እንደ አስተናጋጅ ሀገር፣ ከተለያዩ ሀገራት የሚመጡ መሪዎች ልዑክ እና እንግዶችን ተቀብላ ለማስተናገድና በርካታ ሁለትዮሽ ውይይቶችን ለማድረግ ዝግጁ ናት። የኅብረቱ መቀመጫ እና የአፍሪካ ዲፕሎማሲያዊ ማዕከል የሆነችው አዲስ አበባ ከአህጉሩ እና ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚመጡ መሪዎችን እና የልዑካን ቡድኖችን ተቀብላ ለማስተናገድ ከምንጊዜውም በላይ የተሟላ ዝግጅት አድርጋለች። በአጠቃላይ እንደ መንግስት እነዚህን ሁለት ጉባኤዎች ስኬታማ በሆነ መንገድ ለማስተናገድ የሚከተሉት ዋና ዋና ተግባራት ተከናውነዋል፦ የተቀናጀ አመራር ከመስጠት አንጻር፦ 35 የፌዴራል ተቋማትና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ያሉበት ዐቢይ ኮሚቴ ስራዎቹን በውጤታማነት ሲመራ ቆይቷል። የዲፕሎማሲና መስተንግዶ ዝግጅት፦ ከ180 በላይ በሁሉም የአፍሪካ ኅብረት የሥራ ቋንቋዎች ብቁ የሆኑ የበጎ ፈቃድ ካዴቶች መሰረታዊ ሥልጠና ወስደው ተሰማርተዋል። የመግቢያ ፈቃዶችን ከማሳለጥ አንጻር፦ የቪዛ፣ የጉምሩክና የሚዲያ ፈቃድ አገልግሎቶች በተሳለጠ ሁኔታ እንዲሰጡ ልዩ አሰራር ተዘርግቶ ሥራ ላይ ውሏል። በዚህም ሁሉም የሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ያሉበት ፖርታል ተዘጋጅቶ የሰው ንክኪ በቀነሰ መልኩ በኦንላይን ተከናውነዋል። አገልግሎትን በተመለከተ፦ ሆቴሎች፣ የትራንስፖርት አቅራቢዎችና የታክሲ አሽከርካሪዎች እንግዶችን በኢትዮጵያዊ ጨዋነት ለመቀበል ስልጠና ወስደዋል። እንደ መብራትና ቴሌኮሚኒኬሽን ያሉ መሠረተ-ልማቶችም በላቀ ዝግጁነት ላይ ይገኛሉ። ሰላምና ደህንነት አንጻር፦ የጸጥታና ደህንነት ግብረ-ኃይሉ በቴክኖሎጂና በሰው ኃይል ታግዞ ጉባኤው በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተማማኝ ዝግጅት አድርጓል። ኢትዮጵያ በፓን አፍሪካኒዝም ማዕከልነትና ዲፕሎማሲያዊ ሚና በኩል አህጉሩ የአንድነት ድምጽ እንዲኖረው በማድረግ፣ በሰላም ማስከበር ስምሪቶች ላይ ቀዳሚ ተሳትፎ በማድረግ፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጠና (AFCFTA) ስምምነትን በፍጥነት በማጽደቅ፣ ለተለያዩ የአህጉሪቱ ተቋማት አስፈላጊውን የመሰረተ ልማት በቅረብ ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ ያላት ሀገር ነች። ውድ የሀገራችን ሕዝቦች ይህን ጉባኤ ማዘጋጀት ለእኛ የዲፕሎማሲያዊ ስኬት ማሳያ ብቻ አይደለም ይልቅም አፍሪካውያን ወንድሞቻችን እንደ ሃገር በተፈተንባቸው ወቅቶች ሁሉ ላሳዩን አብሮነት እና ወዳጅነት ምስጋናችንን የምንገልጽበትና አፍሪካዊ አንድነታችንን የምናጸናበት ቋሚ መድረካችን ነው። ኢትዮጵያ አሁን ላይ እያደረገች ባለቸው ሰፊ የሪፎርም ስራ፣ በምግብ ሉአላዊነት፣ በኮሪደር ልማት እና በአረንጓዴ አሻራ ትግበራ ለአፍሪካ ብሎም ለዓለም በምሳሌነት የምትጠቀስ ሃገር ሆናለች። እንደ ስሟ አዲስ እና ውብ እየሆነች የመጣችው አዲስ አበባ በአዳዲስ የከተማ መሰረተ-ልማቶቿ እና እንግዳ ተቀባይ ህዝቧ አህጉር አቀፍና አለም አቀፍ ሁነቶችን የማዘጋጀት ብቃቷ ጎልብቶና ፈክቶ በእጅጉ እያሸበረቀ ይገኛል። ክቡራን የመዲናችን አዲስ አበባ እና ዙሪያ የሚገኙ ከተሞች ነዋሪዎች ይህ ታላቅ አህጉራዊ ኩነት በስኬት እንዲጠናቀቅ የሁሉም ዜጎች የተቀናጀ ትብብር ወሳኝ በመሆኑ እስከ ጉባኤው ፍጻሜ ድረስ በሚኖሩት ጥቂት ቀናት፣ ሊያጋጥሙ የሚችሉ መጠነኛ መስተጓጎሎችን ሀገራችን ከምታገኘው ዘርፈ-ብዙ የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ጥቅም ግንዛቤ ዉስጥ በማስገባት የበኩላቸዉን ደርሻ እንዲወጡ መንግስት ጥሪውን ያቀርባል። በመጨረሻም ይህ ቅድመ-ዝግጅት በተሳካ ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ሌት ተቀን ለሰሩ የፌዴራልና የከተማ አስተዳደር ተቋማት፣ ማህበራት፣ ድርጅቶችና ግለሰቦች ሁሉ በመንግስት ስም የላቀ ምስጋና እናቀርባለን። የመንግሥት ኮሚኒኬሽን አገልግሎት የካቲት 5 ቀን 2018
የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ግብዓቶችን 80 በመቶ በሀገር ውስጥ ማሟላት ተችሏል
Feb 12, 2026 149
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ባለፉት ስድስት ወራት 80 በመቶ ያህሉን የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ግብዓት ከሀገር ውስጥ አቅራቢዎች ማሟላት መቻሉን ገለጸ።   የአገልግሎቱ የኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ አንዋር አብራር እንዳሉት፤ ጥራታቸውን የጠበቁ የተለያዩ ግብዓቶችን ለሀገር ውስጥ አቅራቢዎች ቅድሚያ በመስጠት እንዲያቀርቡ ተደርጓል። ይህም መንግሥት የጀመረውን ሀገር-በቀል ኢኮኖሚን ለማበረታታና የሀገር ውስጥ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት አገልግሎቱ ከወሰዳቸው እርምጃዎች አንዱ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል።   በዚህም መሠረት 3 ሺህ 944 የዲስትሪቢዩሽን ትራንስፎርመሮች፣ ከ32 ሺህ በላይ ኢንሱሌተሮች፣ ከ97 ሺህ በላይ የትራንስፎርመር ፕሮቴክሽን ዕቃዎች፣ ከ32 ሺህ ሜትር በላይ ኮንዳክተርና ኬብሎች እንዲሁም ከ201 ሺህ በላይ የተለያዩ የሀርድዌር ዕቃዎች በሀገር ውስጥ አቅርቦት መሸፈኑን አብራርተዋል።   አገልግሎቱ ለደንበኞቹ ፈጣን ምላሽ ለመስጠትና የግብዓት አቅርቦት ውስንነትን ለመቅረፍ ሀገር-በቀል አምራቾችን እያበረታታ መሆኑንም አረጋግጠዋል። የኢዜአ የዲጂታል ሚዲያ ገጾች https://linktr.ee/ENADigital
በቦንጋ ከተማ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመሸመት እያስቻሉ ነው
Feb 12, 2026 59
ቦንጋ፣ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፦ የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመሸመት እንዳስቻሏቸው የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ የካፋ ዞን ንግድና ገበያ ልማት በበኩሉ ገበያውን ከማረጋጋት ባለፈ ህገወጥ የዋጋ ጭማሪን ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን አስታውቋል፡፡ መንግስት ገበያን ለማረጋጋት እያከናወናቸው ካሉ ዘርፈ ብዙ ተግባራት መካከል በየአካባቢው የተቋቋሙ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በእነዚህ ገበያዎችም በህብረተሰቡ ላይ ሲደርስ የነበረውን የኑሮ ጫና መቀነስ የተቻለ ሲሆን የግብርና ምርቶችም በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እንዲቀርቡ ዕድል ፈጥሯል፡፡ በካፋ ዞንም ቦንጋ ከተማን ጨምሮ በዘጠኝ የዞኑ ከተሞች የሰንበት ገበያን በማቋቋም ህብረተሰቡ የተለያዩ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ እየተሰራ ነው፡፡ ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች እንደገለጹት የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ አስችሏቸዋል፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወይዘሮ ወይኒቱ ወዳጆ በከተማው የተቋቋመው የቅዳሜና እሁድ ገበያ የአትክልትና ሌሎች የግብርና ምርቶችን በቅናሽ ዋጋ ለመሸመት እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። መንግስት ገበያን ለማረጋጋት እየወሰዳቸው ያሉ የመፍትሔ እርምጃዎች የህብረተሰቡን ጫና እያቃለለ በመሆኑ ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ብለዋል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ አስራት አኢሮ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች መስፋፋታቸው በተለይ ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የማህበረሰብ ክፍሎች ትልቅ እፎይታ ፈጥረዋል። ገበያዎቹ የፈለጉትን ምርት በጥራትና በብዛት በአንድ ቦታ ለማግኘት እንዳስቻሏቸው የገለፀችው ደግሞ ሌላኛዋ የከተማው ነዋሪ ስምረት ቆጭቶ ናት። የገበያ አማራጩ የዋጋ ጭማሪን በማስቀረት የተረጋጋ ገበያ እንዲኖር ማስቻሉን ጠቅሳ፣ በቀጣይ ከግብርና ምርቶች ባሻገር የፋብሪካ ምርቶችም በተመሳሳይ ለህብረተሰቡ እንዲቀርቡ ጠይቃለች። የካፋ ዞን ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ምክትል ሃላፊ አቶ ሃብታሙ ገብረስላሴ በበኩላቸው በአምራችና ሸማች መካከል ያለውን ሰንሰለት በማሳጠር ገበያን ለማረጋጋትና ህገወጥ ንግድን ለመከላከል በቅንጅት የተሰራው ሥራ ውጤት እያመጣ ነው ብለዋል፡፡ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን በማቋቋም በማህበራት አማካኝነት የተለያዩ የግብርና ምርቶች ለሸማቹ ማህበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ መሆኑን ገልጸው፣ በዚህም ያልተገባ የዋጋ ጭማሪን ለመከላከል ተችሏል ብለዋል። ገበያዎቹ የዋጋ ንረትን በመከላከል የህብረተሰቡን ጫና እየቀነሱ በመሆኑ ቀጣይነታቸውን ለማረጋገጥና ለማዘመን የዞኑ አስተዳደር በ18 ሚሊዮን ብር በቦንጋ ከተማ ሼድ እያስገነባ መሆኑንም ጠቁመዋል። የገበያ አማራጮችን ከማስፋፋት ባለፈ የመንግስት ሠራተኞች ሸማች ማህበራትን በማደራጀትና 3 ሚሊዮን ብር ብድር በማመቻቸት ወደ ሥራ ለማስገባት እየተሰራ መሆኑንም አስታውቀዋል። ባለፉት ስድስት ወራትም ከዘጠኝ ሺህ በላይ የንግድ ተቋማት ላይ ክትትል በማድረግ ያለአግባብ ዋጋ በጨመሩና ህገ ወጥ ድርጊት በፈጸሙ 1ሺህ 865 የንግድ ተቋማት ላይ እርምጃ መወሰዱን ተናግረዋል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም