ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በክልሉ የግብርና ሥራን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው
Jul 11, 2026 49
ወላይታ ሶዶ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና ሥራን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢዎች ልማት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በወላይታ ዞን ዱጉና ፋንጎ ወረዳ ከ21 ሚሊዮን 500 ሺህ ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባውን የብላቴ ኤታ መስኖ አውታር ለአገልግሎት አብቅቷል።   በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የቢሮው ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር እንደገለጹት፤ በክልሉ የመስኖ አውታሮችን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሠራ ይገኛል። ይህም አርሶ አደሩን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ በዓመት ሁለትና ሦስት ጊዜ በማምረት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ ይገኛል ብለዋል።   ዛሬ የተመረቀው ፕሮጀክትም ከ1 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት የማልማት አቅም ያለው ሲሆን፤ ከ1 ሺህ 200 በላይ አርሶ አደሮችን ቀጥተኛ ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ኃላፊው አብራርተዋል። የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ በበኩላቸው፤ በዞኑ የሚገኙ አርሶ አደሮች ያሉትን የውኃ አማራጮች በመጠቀም በመስኖ እንዲያለሙ በተደረገው ጥረት ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል።   ሥራው አርሶ አደሩን ከተረጂነት በማላቀቅ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ ትልቅ አቅም መፍጠሩን ጠቅሰዋል፡፡ የዱጉና ፋንጎ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘካሪያስ ዎንታሞ በበኩላቸው፤ በወረዳው ሰፊ ሊለማ የሚችል የእርሻ መሬት መኖሩን ጠቅሰው፣ አርሶ አደሮች በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ በማልማት ወደተሻለ የኑሮ ደረጃ እየተሸጋገሩ መሆኑን ተናግረዋል።   ዛሬ የተመረቀው የመስኖ ፕሮጀክትም የሦስት ቀበሌ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የብላቴ ኤታ እና የፓንጎ ቢጆ ቀበሌ አርሶ አደሮች፤ ቀደም ሲል የዝናብ ወቅትን ብቻ በመጠበቅ በዓመት አንድ ጊዜ ያመርቱ እንደነበርና ኑሯቸውም ከእጅ ወደ አፍ እንደነበር አስታውሰዋል። ከዚህ በኋላ በመስኖው በመታገዝ ሰብል እንዲሁም አትክልትና ፍራፍሬዎችን በማምረት ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተናግረዋል።
በምዕራብ እና ምስራቅ ሐረርጌ ዞኖች የሚገኙ ፓርኮችን የቱሪዝም መዳረሻነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው
Jul 11, 2026 51
፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብና ምስራቅ ሐረርጌ ዞኖች የሚገኙ ሦስት ፓርኮችን በማልማትና በማስተዋወቅ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸውን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ደንና ዱር እንስሳት ድርጅት አስታወቀ። የኦሮሚያ ክልል ደንና ዱር እንስሳት ድርጅት የሐረርጌ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ ፋኪያ ጀማል ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ ከተቋቋሙት አዳዲስ ፓርኮች ሁለቱ በምዕራብ ሐረርጌ ዞን፣ አንዱ ደግሞ በምስራቅ ሐረርጌ የሚገኝ ነው።   በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ገመቺስ እና አንጫር ወረዳዎች የተቋቋሙት የባሬሞ እና የድንድን ፓርኮች የደን ይዘት እና የዱር እንስሳት መጠን ለማሳደግ የተፈጥሮ ዛፍ ችግኞችን በብዛት የመትከል፣ ደኑን የመጠበቅና የመንከባከብ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን አመልክተዋል። በዚህ ወቅትም የፓርኮቹ የደን መጠን እያደገ በመምጣቱም እንደ አጋዘን፣ ከርከሮ፣ ድኩላ፣ ጉሬዛና ሌሎች የዱር እንስሳት ቁጥር እየጨመረ መምጣቱንም ተናግረዋል። በደኖቹ ውስጥ ከሚገኙ እንደ አጋዘን ካሉ እንስሳት ሕጋዊ አደን ገቢ እየተገኘ መሆኑን ገልጸው፣ ከዚህም የአካባቢው አርሶ አደሮች ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። በዚህ ዓመት ከእንስሳት አደን ከተገኘው ገቢ ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆነው በደን እንክብካቤ ለተሰማሩ የአካባቢው አርሶ አደሮች መሰጠቱን አብራርተዋል። በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ኩርፋ ጨሌ ወረዳ የተቋቋመው የደባል ሞቲ ጋራ ፓርክ በታሪካዊ ስፍራነቱና በተራራማ አቀማመጡ ለቱሪዝም ልማት ለማዋል የማስተዋወቅ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በጽሕፈት ቤቱ የፓርኮች እና ኢኮ ቱሪዝም ባለሙያ አቶ ጀቤሳ ፊጡማ በበኩላቸው፣ በምስራቅ ሐረርጌ ዞን የኩርፋ ጨሌ፣ ቀርሳ፣ ገረዋ እና በደኖ ወረዳዎችን የሚያዋስነው የደባል ሞቲ ጋራ ፓርክን በስፋት በማስተዋወቅና በማልማት የቱሪዝም መስህብነቱን ለማሳደግ እየተሠራ ነው ብለዋል።   ከምስራቅ ሐረርጌ ዞን በተጨማሪም ከድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር እና ሐረሪ ክልል ጋር በመሆን በተለያዩ ዘዴዎች የማስተዋወቅ ሥራ እየተሠራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከባሕር ጠለል በላይ 3 ሺህ 440 ሜትር ከፍታ ያለው ደባል ሞቲ ጋራ በተፈጥሯዊ አቀማመጡ የጎብኚዎችን ዓይን የሚስብ መሆኑን ገልጸው፤ በዚህም ፓርኩን ለሀገር ውስጥና ውጭ ጎብኚዎች ምቹ ለማድረግና የአገልግሎት መስጫ ሎጆችን ለመገንባት ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። የኦሮሚያ ደንና ዱር እንስሳት ድርጅት የሐረርጌ ቅርንጫፍ በምዕራብና ምስራቅ ሐረርጌ ዞኖች ፓርኮች፣ የኢኮ ቱሪዝምና የተለያዩ መስህቦችን ያካተተ ከ77 ሺህ ሄክታር በላይ የደን ክልል ያስተዳድራል።
መንግስት ያመቻቸልንን የስራ ዕድል በመጠቀም ባስፋፋነው ስራ ሌሎችን ተጠቃሚ ማድረግ ችለናል
Jul 11, 2026 108
ሀዋሳ ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦መንግስት ያመቻቸላቸውን የስራ ዕድል በመጠቀም ባስፋፉት ስራ ሌሎችን ተጠቃሚ እያደረጉ መሆናቸውን በሲዳማ ክልል ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ገለጹ፡፡ የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ በተፈጠረው ምቹ የሥራ ዕድል ተጠቅመው በርካቶችን ወደ መቅጠር የደረሱ ስራ ፈጣሪዎች መኖራቸውን ጠቅሶ፣ በቀጣይም ይህ ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጿል። ወጣቶቹ እንደገለፁት፤ መንግስት ባመቻቸላቸው የብድርና የመስሪያ ቦታ በመጠቀም ስራቸውን በማስፋፋት ለሌሎች የስራ ዕድል ፈጥረዋል። በክልሉ በአለታ ወንዶ ከተማ የ”ጊዮን ሻማ አምራቾች ማህበር” አባል ወጣት ኤደን ማቲዎስ እንደገለጸችው፤ በተሰጣቸው አጭር የሥራ ፈጠራ ስልጠና፣ መነሻ ብድር፣ የባንክ ብድር አቅርቦት እንዲሁም የመስሪያና መሸጫ ቦታ ታግዘው አምስት ሆነው ወደ ሻማ ማምረት ሥራ መግባታቸውን ገልጻለች። ወደ ሥራ ከገባ ሦስት ዓመት የሆነው ማህበሩ ስኬታማ በመሆን ከመንግሥት የወሰዱትን 150 ሺህ ብር ብድር መመለሱንና ለ10 ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር አሁን ላይ አጠቃላይ ሀብታቸው ወደ አንድ ሚሊዮን ብር መድረሱን ተናግራለች። ከተስፋ መቁረጥ ሕይወት ወጥተው ዛሬ ላይ ከራሳቸው አልፈው ቤተሰብንና ሌሎችን ወደ መቅጠር መድረሳቸውን ገልጻ፤ ወጣቶች የመንግሥትን ድጋፍ እንደ መነሻ በመጠቀም በትጋት በመስራት መለወጥ እንደሚችሉ አመልክታለች።   ሌላው በጩኮ ከተማ በአገልግሎት ዘርፍ በመሰማራት ውጤታማ መሆናቸውን የተናገረው የ”እያየን ካፌና ጌም ዞን ማህበር” ሰብሳቢ ወጣት ሳሙኤል ተስፋ፤ መንግሥት ባመቻቸላቸው የ200 ሺህ ብር ብድርና የመስሪያ ቦታ ታግዘው ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግሯል። ሥራቸው በአጭር ጊዜ ውጤታማ በመሆኑ በሕይወታቸው ለውጥ ማየታቸውንና ለ32 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ጠቅሶ፣ አሁን ላይ አጠቃላይ ሀብታቸው ከ8 ሚሊዮን ብር በላይ መድረሱን ነው የገለጸው። በሐዋሳ ከተማ አስተዳደር እየተካሄደ ባለው የ4ኛው ዙር የኮሪደር ልማት ስራ በአረንጓዴ ልማት ተደራጅተው እንዲሰማሩ አስተዳደሩ ባመቻቸላቸው ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገረው ደግሞ ወጣት ግዛው ግርማ ነው። በሚያገኙት ገቢ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን እየደገፉ ሲሆን፤ አሁን ላይ ወጣቱን በልማት በማሳተፍ በፍትሐዊነት ተጠቃሚ ለማድረግ መንግሥት እያደረገ ባለው ጥረት መደሰቱንም ተናግሯል። የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ከፍያለው ከበደ፤ በክልሉ በከተማና በገጠር ያሉትን አማራጮችና ጸጋዎችን በተቀናጀ መንገድ በመጠቀም፣ የወጣቱን የሥራ ዕድል ፈጠራ ለማጠናከር የተደረጉ ጥረቶች ውጤታማ ናቸው ብለዋል።   በተለይ የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ዕድሎችን በማስፋት ረገድ መንግሥት የሰጠው ትኩረት ውጤት እያስገኘ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
የአርባ ምንጭን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት አቅሞች በመለየት በአጭር ጊዜ ውስጥ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የሚያስደንቁ ናቸው
Jul 11, 2026 94
አርባ ምንጭ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ የአርባ ምንጭን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት አቅሞች በመለየት በአጭር ጊዜ ውስጥ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የሚያስደንቁ መሆናቸውን የከተማዋ ነዋሪዎች ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሰሞኑን በአርባ ምንጭ ከተማና አካባቢው በመገኘት የገጠር ኮሪደርን ጨምሮ በከተማዋ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን መርቀው ስራ አስጀምረዋል። በቆይታቸው የተለያዩ የልማት ስራዎችን ተዘዋውረው የጎበኙ ሲሆን በአርባ ምንጭ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ከሀገርም ባለፈ ለጎረቤት ሀገራት ጭምር የሚጠቅሙ መሆናቸውን ተናግረዋል።   በከተሞችም ይሁን በገጠር ዜጎችን የሚጠቅሙና ሀገርን የሚለውጡ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን አንስተው ለኢትዮጵያ እድገትና ብልጽግና ስኬት የመንግስት ጥረት ይቀጥላል ብለዋል። በአርባ ምንጭ የተከናወኑ የልማት ፕሮጀከቶችን በተመለከተ ኢዜአ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች የአርባ ምንጭን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት አቅሞች በመለየት በአጭር ጊዜ ውስጥ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የሚያስደንቁ መሆናቸውን አንስተዋል። ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል አቶ ተዘራ ቀፃዮ፤ በአርባ ምንጭ ከተማና አካባቢዋ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተገንብተውና ተጠናቀው ለአገለግሎት የበቁ ፕሮጀክቶች የመንግስትን የልማት ትጋት በተግባር የሚያሳዩ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሌላኛዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ ድንበሯ ቱሉ፤ አርባ ምንጭ ከተማ ከተቆረቆረች ረጂም ዓመታት ቢሆናትም ልማት እና እድገቷ እምብዛም እንደነበር አንስተዋል። በቅርቡ የተከናወኑ የልማት ስራዎች ግን እስካሁን ለምን መስራት አልተቻለም የሚል ቁጭት የሚፈጥሩ ስለመሆናቸው ተናግረው በዚህ ረገድ መንግስት እያደረገ ላለው ጥረት አመስግነዋል። በከተማዋ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ እየተገነቡ ያሉ የልማት ስራዎች የከተማዋን ዕድገት ከማፋጠን ባለፈ ለጉብኝትም ይሁን ኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት ነው ብለዋል። የከተማዋ ዕድገትና የሚታየው ለውጥ ለእንግዶች ብቻ ሳይሆን ለነዋሪዎችም አስደናቂ መሆኑን ተናግረው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ለማስቀጠል ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል። አቶ ግርማ ጉንሤ የተባሉ አስተያየት ሰጪ በበኩላቸው የአርባ ምንጭ ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ለኑሮ ምቹ እና ጽዱ ከማድረግ ባለፈ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴን እያሳለጠ መሆኑን ገልጸዋል።   በከተማዋ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ከተማዋ ባላት ፀጋ ልክ እንድታድግ እያስቻላት ነው ያሉት ደግሞ የአርባ ምንጭ ከተማ ከንቲባ መስፍን መንዛ (ዶ/ር) ናቸው። ሰው ተኮር እሳቤ ያለው የለውጡ መንግስት ከተሞችን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የሰነቀው ራዕይ የአርባ ምንጭ ከተማ ፀጋዎች ተገልጠው ወደ ሀብትነት እንዲቀየሩ ማስቻሉን ጠቅሰዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ እየተገነባ ያለው ከ20 ኪሎ ሜትር በላይ የተቀናጀ የኮሪደር ልማት አብዛኛው እየተጠናቀቀ እንደሚገኝም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የፋይናንስ ተደራሽነትን በማስፋትና በዘርፉ የሴቶችን አመራርነት ለማሳደግ እየሰራ ነው
Jul 11, 2026 250
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የፋይናንስ ተደራሽነትን በማስፋትና የሴቶች አመራር ውክልናን በማሳደግ የፋይናንስ አካታችነትን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ መሆኑን የባንኩ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በሁሉም ባንኮች ያለውን የሴቶች የፋይናንስ አካታችነት በየጊዜው መሻሻሉን መከታተል የሚያስችለውን ሁለተኛውን የሴቶች የፋይናንስ አካታችነት ስኮርካርድ ይፋ አድርጓል። እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ኢኒሼቲቭ የሆነው የኢትዮጵያ ሴት የፋይናንስ ባለሙያዎች ኔትወርክ- (NEWFin) በአመራርና በመሠረታዊ የፋይናንስ ትምህርት የሰለጠኑ አንድ ሺህ ወጣት ሴት የፋይናንስ ባለሙያዎችን አስመርቋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ በሁለተኛው የሴቶች የፋይናንስ አካታችነት ስኮርካርድ ግምገማ 32 የሚሆኑ ባንኮች ማለፋቸውን ገልጸዋል። በዚህም የሴቶች የፋይናንስ ተጠቃሚነት ከባለፈው ዓመት መሻሻል ማሳየቱን አንስተው፣ አሁንም ይበልጥ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በትኩረት መስራት እንደሚገባ አመልክተዋል። በቀጣይም የብድር መጠን ክፍፍልን ማሳደግና የስራ ፈጠራን ማቀላጠፍ ላይ ማተኮር እንደሚገባ አስታውቀዋል። የዘምዘም ባንክ ዋና ስራ አስኪያጅ እና የኒውፊን (NEWFin) ሊቀ-መንበር መሊካ በድሪ በበኩላቸው፤ ዛሬ የተመረቁት አንድ ሺህ ወጣት ሴት የፋይናንስ ባለሙያዎች የነገ የፋይናንስ ዘዋሪዎችና አመራሮች መሆናቸውን ገልጸዋል። አካታች የሆነ የፋይናንስ ስርዓት ለመፍጠር ያለንን ቁርጠኝነት በማጠናከር የበለጸገች ሀገር ለመገንባት በጋራ እንሰራለን ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ግብርን በወቅቱ በመክፈል የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ የበኩላችንን እየተወጣን ነው
Jul 11, 2026 204
ሆሳዕና፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱ በመክፈል በአካባቢው የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን የሆሳዕና ከተማ ግብር ከፋዮች ገለፁ። የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ጽሕፈት ቤት በ2019 በጀት ዓመት ከ3 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ከመደበኛና ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ለመሰብሰብ አቅዶ ወደ ተግባር መግባቱንም አስታውቋል። የከተማዋ ግብር ከፋዮች እንደገለፁት፤ ግብርን በወቅቱ መክፈል ለልማት ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ በማግኘት ተጠቃሚ ለመሆን ያስችላል። በከተማው የአራዳ ቀበሌ ነዋሪና የደረጃ "ሀ" ግብር ከፋይ አቶ ፀጋዬ በላቸው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱ በመክፈል በአካባቢው የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ አድርገዋል። በከተማው የሴች ዱና ቀበሌ ነዋሪዋና የደረጃ "ለ" ግብር ከፋይ ሐኒያ ኤልያስ በበኩሏ፤ የከተማውን ነዋሪዎች ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግራለች። የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ግብርን በወቅቱ መክፈል የልማት ጥያቄን ለመመለስና ከራስ ለራስ ልማት የሚውል በመሆኑ፣ የዜግነት ግዴታዋን መወጣት ስለመቻሏም ገልጻለች። በከተማው የሕዝብን ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ ግብር ከፋዩ ማኅበረሰብ የሚጠበቅበትን ግብር በወቅቱ መክፈል አለበት ያሉት ደግሞ የደረጃ "ለ" ግብር ከፋይ የሆኑት አቶ ኤፍሬም አበራ ናቸው። ግብርን በወቅቱ መክፈል በሥነ ምግባር የታነጹ ዜጎችን ለማፍራት የሚረዱ የትምህርት ተቋማትን ለማስፋፋት፣ ጽዱ፣ ውብና ማራኪ አካባቢን ለተተኪው ትውልድ ለማስተላለፍ ያለው ሚና ከፍተኛ ስለመሆኑም አስረድተዋል። የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አውላቸው ዮሐንስ እንደገለፁት፤ በከተማው የገቢ አማራጭን በማስፋት የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰሩ ባሉ ሥራዎች ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል። ጽሕፈት ቤቱ በ2018 በጀት ዓመት ከመደበኛና ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች ከ2 ነጥብ 36 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። በ2019 በጀት ዓመት ከመደበኛና ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ከ3 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ትግበራ መገባቱንም ገልጸዋል።
የኑሮ ውድነትን ማረጋጋት የሚያስችሉና የገበያ ተደራሽነትን የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jul 11, 2026 248
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ የኑሮ ውድነትን ማረጋጋት የሚያስችሉና የገበያ ተደራሽነትን የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸሙን የሚገመግም የሴክተር ጉባኤ በሀዋሳ ያካሄደ ሲሆን፣ በቀጣይ በጀት ዓመት የትኩረት ነጥቦች ላይም ውይይት ተደርጓል።   ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደተናገሩት የንግድ ዘርፉን በማዘመን በኩል የተከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ጊዜንና ጉልበትን የሚቆጥቡ የዲጂታል አማራጮችን የማስፋት ሥራ በትኩረት መሰራቱንና አበረታች ውጤት መመዝገቡን ጠቅሰው የተገኙ መልካም ውጤቶች እንዲሰፉ ይደረጋል ብለዋል። የሸማቹንና ሻጩን በቀጥታ በማገናኘት ገበያን በማረጋጋት በኩል ቁልፍ ሚና እየተጫወቱ የሚገኙ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን የማጠናከርና ደረጃቸውን የማሻሻል ሥራም በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። የግብይት ማዕከላትን የማስፋት፣ የምርት ጥራትና ዋጋን ማዕከል ያደረገ የገበያ ቁጥጥር በአዲሱ በጀት ዓመት በልዩ ትኩረት ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል መሆኑንም አንስተዋል። በተጨማሪም የኑሮ ውድነትንና ገበያን ማረጋጋት የሚያስችሉ፣ የገበያ ተደራሽነትን የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ ነው ያሉት። ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል የአፋር ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ አህመድ አብዱልቃድር በክልሉ የገበያ ተደራሽነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት አበረታች መሆናቸውን ገልጸዋል።   በቀጣይም የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ደረጃቸውን ለማሻሻል በትኩረት ይሰራል ብለዋል። በክልሉ በበጀት ዓመቱ በንግድ ዘርፉ በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት ለመስጠት የተደረጉ ጥረቶች ስኬታማ መሆናቸውን ያነሱት ደግሞ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ባዩሽ ተስፋዬ (ዶ/ር) ናቸው።   በክልሉ ከ190 በላይ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች መገንባታቸውን አንስተው በተያዘው በጀት ዓመት ይህንን የማስፋት ሥራ ይሰራል ሲሉ ገልጸዋል።
በቡና ልማት ላይ የተደረገልን ሙያዊ ድጋፍ ተጠቃሚ አድርጎናል -አርሶ አደሮች
Jul 11, 2026 319
ነቀምቴ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን ባለፉት ዓመታት የቡና ልማትን ለማሳደግ የሚደረገው ድጋፍና ሙያዊ እገዛ ተጠቃሚ አድርጎናል ሲሉ ቡና አምራች አርሶ አደሮች ተናገሩ። በዞኑ የጉቶ ጊዳ ወረዳ አርሶ አደር ሀብታሙ ፍቃዱ፤ "ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ለቡና ምርት በተሰጠው ትኩረትና የሚደረገውን ሙያዊ ድጋፍን በመጠቀም ጥራቱን የጠበቀ ምርት ማምረት ጀምረናል፤ በዚህም ይበልጥ ተጠቃሚ እየሆንን ነው" ብለዋል። በአሁኑ ወቅት የቡና ምርት ልማትና ጥራት በየጊዜው እያደገ በመምጣቱ፣ ጥራቱን የጠበቀ ምርት በማቅረብ በገበያው ተወዳዳሪ ለመሆን እየሰሩ መሆኑንም ተናግረዋል። በቀጣይም በዓለም ገበያ ተፈላጊ የሆኑ የቡና ዝርያዎችን በማልማት ስራቸውን ይበልጥ ለማሻሻል ማቀዳቸውን ገልጸዋል።   ሌላኛው የቢሎ ቦሼ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ደረጄ አርፍሳ በበኩላቸው፤ ዘንድሮ ያረጁ የቡና ተክሎችን በመንቀል እና በመጎምደል እንዲሁም አዳዲስ ምርጥ ዝርያ ያላቸው ችግኞችን እየተከሉ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በጥራት መጓደል ምክንያት በሚያመርቱት ልክ ለገበያ ማቅረብ እንዳልቻሉ ያስታወሱት አቶ ደረጄ፣ አሁን ላይ ግን ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን ማቀዳቸውን ጠቁመዋል። የምስራቅ ወለጋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት የቡናና አትክልት ልማት ቡድን መሪ አቶ አስፋው መኮንን በበኩላቸው፤ በዞኑ በየደረጃው በተሰጠ ስልጠና እና በተደረገ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ፣ ጥራቱን የጠበቀ ቡና እየተመረተ መሆኑን ተናግረዋል።   አርሶ አደሮች ከተከላ እስከ ምርት አሰባሰብ ያለውን የጥራት አጠባበቅ ሂደት እንዲረዱ እና በቴክኖሎጂ የተደገፈ የአመራረት ስልትን በመጠቀም ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ ትኩረት መደረጉንም ገልጸዋል። ከ96 ሄክታር በላይ መሬት ላይ የሚገኝ ያረጀ ቡና ተነቅሎ በአዲስ ችግኝ የተተካ ሲሆን፣ 320 ሄክታር መሬት ላይ የሚገኝ ያረጀ ቡና ደግሞ መጎንደሉን ተናግረዋል። ዘንድሮም በመንግስትና በግል የቡና ችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች ከ300 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኝ የተዘጋጀ ሲሆን፣ የተከላ ስራውም እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።
በባሌ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራ አማራጮችን በማስፋት የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል
Jul 11, 2026 369
ሮቤ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራ አማራጮችን በማስፋት የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተሰሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት መታየቱን የዞኑ የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከ89 ሺህ 500 ለሚበልጡ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩ ተመላክቷል። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ተሾመ ለሚ በተለይ ለኢዜአ እንዳሉት፣ በዞኑ የሥራ ዕድል ፈጠራ አማራጮችን በማስፋት የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተሰሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት ተገኝተዋል።   በዞኑ በተያዘው የበጀት ዓመት ከ89 ሺህ 500 ለሚበልጡ ወጣቶች በተለያዩ መስኮች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል። ወጣቶቹ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው በከተማ ግብርና ልማት፣ በእንጨትና ብረታ ብረት፣ በዶሮና እንስሳት እርባታ ዘርፎች መሆኑን ገልጸዋል። ወጣቶቹ በተሰማሩባቸው የሥራ መስኮች ውጤታማ እንዲሆኑ ከ964 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር የተመቻቸላቸው ሲሆን፣ 4 ሺህ 540 ሄክታር የእርሻ መሬት እንዲያኙ መደረጉን አክለዋል። ለእነዚሁ በእርሻ ሥራ የተሰማሩ ወጣቶች በተመቻቸው ብድር በመጠቀም 50 የእርሻ ትራክተሮች የተገዙላቸው መሆኑን አመልክተዋል። የአጋርፋ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አብዱልቃድር ኡስማን በበኩላቸው፣ በወረዳው የከተማ ግብርናና የጎጆ ኢንዱስትሪ ኢኒሼቲቭ የበርካታ ወጣቶች የገቢ ምንጭ እየሆነ መጥቷል ብለዋል።   በወረዳው በበጀት ዓመቱ በዘርፉ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለሆኑ 10 ሺህ ለሚበልጡ ወጣቶች ከ185 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር እንዲያገኙ መደረጉን ተናግረዋል። በአጋርፋ ወረዳ የሥራ ዕድል ተጠቃሚዎች መካከል አደም አብደላ በሰጠው አስተያየት፣ በእንጨትና ብረታ ብረት ሥራ በመሰማራት ውጤታማ በመሆን ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ተናግሯል። በቀጣይም ወደ ተሻለ የኢንቨስትመንት ዘርፍ ለመሸጋገር ጠንክሮ እንደሚሠራ ገልጿል።   በከተማው በወተት ላሞች እርባታ በመሰማራት ውጤታማ እየሆነ መምጣቱን የተናገረው ደግሞ ወጣት አብዱለጢፍ አብዱልመናን ነው። በሥራው ውጤታማ በመሆን ቤተሰቡን ከማስተዳደር ባለፈ ጥሪት ማፍራት መጀመሩን ተናግሯል። በባሌ ዞን ባለፈው የበጀት ዓመት 75 ሺህ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሮ እንደነበር ተጠቅሷል።
በከተማው በአዲሱ በጀት ዓመት 12 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደተግባር ተገብቷል
Jul 10, 2026 773
‎‎ሀዋሳ፤ ሐምሌ3/2018(ኢዜአ)፡-በሀዋሳ ከተማ አስተዳደር በአዲሱ በጀት ዓመት 12 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደተግባር መገባቱን የከተማ አስተዳደሩ ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በከተማው ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የነዋሪዎችን የመሠረተ ልማት እና የአገልግሎት አቅርቦት ጥያቄዎች ለመመለስ ትኩረት መሰጠቱም ተመላክቷል። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ መልኩ ማርቆስ ለኢዜአ እንደገለጹት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በከተማው ከ7 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ የዕቅዱን 102 ፐርሰንት ማሳካት ተችሏል፡፡ በ2019 ግብር ዘመን12 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደተግባር መገባቱን ገልፀው ከሐምሌ 1 ጀምሮ ገቢ የመሰብሰብ ሥራው መጀመሩን ጠቅሰዋል፡፡   ባለፉት ሁለት ዓመታት የገቢ አሰባሰብ ሥራው በቴክኖሎጂ መታገዙ፣ የባለሙያዎች አቅም መገንባቱና የገቢ ምንጮችን ማስፋት በመቻሉ ገቢን ማሳደግ ተችሏል ብለዋል፡፡ በተያዘው የግብር ዘመንም የተጨማሪ እሴት ታክስ ገቢን የማሳደግ፣ ከቅጥር የሚገኝ ገቢን እና የአከራይ ተከራይ ገቢን አሟጦ የመሰብሰብ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አቶ መልኩ አስረድተዋል፡፡ በከተማ አስተዳደሩ ካለፉት ሁለት ዓመታት ጀምሮ ከጥሬ ገንዘብ ንክኪ ነፃ የሆነ የገቢ አሰባሰብ ሥርዐት በመዘርጋት በባንክ የክፍያ ማረጋገጫ ብቻ ገቢ እየተሰበሰበ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ ከዚህ ዓመት ጀምሮም የባንክ ክፍያን በማስቀረት በቴሌ ብር፣ በሞባይል ባንኪንግ እና ሌሎች ዘመናዊ የክፍያ አማራጮች ብቻ ገቢን ለመሰብሰብ የሚያስችሉ ቅድመ ዝግጅቶች ተደርገው ወደ ሥራ መገባቱን አስረድተዋል፡፡ በከተማው ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የነዋሪዎችን የመሠረተ ልማት እና የአገልግሎት አቅርቦት ጥያቄዎች ለመመለስ ትኩረት መሰጠቱንም አመልክተዋል። ከሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ እየተካሄደ ባለው የገቢ አሰባሰብ ሂደት ግብር ከፋዮች ግብራቸውን እየከፈሉ እንደሚገኙም አቶ መላኩ ጠቁመዋል፡፡   ከእነዚህ መካከል በታቦር ክፍለ ከተማ በሸቀጣሸቀጥ ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩት ወይዘሮ መስከረም አስፋው በየዓመቱ ግብራቸውን በወቅቱና በታማኝነት የመክፈል ልምድ እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡ ከዜጎች የሚሰበሰበው ገቢ በከተማዋ ለሚከናወኑ የልማት ሥራዎች እንደሚውል በመረዳታቸው በራሳቸው ተነሳሽነት ግብራቸውን በወቅቱ እንደሚከፍሉ ተናግረዋል፡፡ በግብር ሰብሳቢው አካል የሚሰጠው አገልግሎት በቴክኖሎጂ የታገዘና ከጊዜ ወደ ጊዜ ቅልጥፍናው እየጨመረ የመጣ በመሆኑ ያለ እንግልት ግብራቸውን በቀላሉ መክፈል እንደቻሉም ጠቁመዋል፡፡   በሀዋሳ መናኸሪያ ክፍለ ከተማ በእንግዳ ማረፊያ የአገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ኢያሱ በገጄ ግብር ለሀገራችን የምንከፍለው የዜግነት ግዴታችን ነው ብለዋል፡፡ የከተማዋ የልማት ሥራ ጥቅሙ ለነዋሪው እንደሆነ ጠቅሰው ልማቱ እንዲፋጠን ግብራቸውን በአግባቡና በወቅቱ በመክፈል ሀላፊነታቸውን እየተወጡ መሆኑን ገልፀዋል፡፡  
ቢሮው የአገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የተገልጋዩን እርካታ ማሳደግ ችሏል
Jul 10, 2026 649
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):-የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ የአገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ በመደገፍና አዳዲስ አሰራሮችን በመዘርጋት የተገልጋዩን እርካታ ማሳደግ መቻሉን አስታወቀ። ቢሮው በ2018 በጀት ዓመት የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት ያከናወናቸውን ተግባራት፣ የቢሮውን የለውጥ ጉዞና የተገኙ ስኬቶችን የሚያሳይ ኤግዚቢሽንም በዛሬው ዕለት በይፋ ከፍቷል።   የቢሮው የጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳነ ሱሌ በኤግዚቢሽኑ መክፈቻ ላይ እንደገለጹት፤ ቢሮው የግብር ከፋዩን እንግልት ለመቀነስና ግልጽነትን ለመፍጠር በርካታ የሪፎርም ስራዎችን አከናውኗል። ወደ 24 የሚጠጉ አሰራሮች መዘርጋታቸውን ይህንንም በማሳተም ለተገልጋዩ ማህበረሰብ ተደራሽ መደረጉንና ከግብር ከፋዩ ሕብረተሰብ ጋር ተደጋጋሚ ውይይቶች መደረጋቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት መሰራቱን ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት በቢሮው ስር ባሉ 17ቱም ቅርንጫፎች የሚገኙ ከሰባት ሺህ በላይ ሰራተኞችን መቆጣጠር የሚያስችል የቴክኖሎጂ አሰራር መዘርጋቱን ጠቁመዋል፡፡ በዚህም የአገልግሎት አሰጣጡ እንዴት እየተከናወነ እንደሚገኝ ዋና ቢሮ ሆኖ በቀጥታ መከታተል የሚያስችል የቁጥጥር ስርዓት መዘርጋቱንም ጠቁመዋል፡፡ በኤግዚቢሽኑ መክፈቻ ስነ-ስርዓት ላይ የተገኙት የአዲስ አበባ የንግድ እና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ዘሃራ መሐመድ በበኩላቸው፤ ከቢሮው ጋር እየተደረገ ያለው የተቀናጀ አሰራር አዎንታዊ ውጤት እያመጣ መሆኑን ገልጸዋል።   በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ በተደረገው የጋራ ጥረትና ቅንጅታዊ አሰራር፣ ከነጋዴው ማህበረሰብ የተነሱ የተለያዩ ቅሬታዎችን በጋራ በመገምገም 620 ለሚሆኑ ነጋዴዎች ለገጠሟቸው ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ እንዲያገኙ ማድረግ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡      
ተምሳሌቶቹ የቢሾፍቱ ከተማ የሌማት ትሩፋት ተጠቃሚዎች
Jul 10, 2026 550
የሌማት ትሩፋት ሀገራዊ ውጤት እና በመርሃ ግብሩ ህይወታቸውን ያሻሻሉ የቢሾፍቱ ነዋሪዎች ለብዙ ኢትዮጵያውያን ወተት፣ እንቁላል፣ ማርና ሥጋ በምግብ ገበታ የማይገኙ፣ ለረጅም ዓመታት የቅንጦት ያህል የሚታዩና በቂ ምርት ባለመኖሩም በገበያ ላይ በስፋት የማይገኙ ነበሩ። ይህንን እውነታ ለመቀየርና የዜጎችን የሥርዓተ ምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ጥቅምት 24 ቀን 2015 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተጀመረው የሌማት ትሩፋት ሀገራዊ መርሃ ግብር ዛሬ ላይ ትልቅ ተስፋና ተጨባጭ ውጤት እያሳየ ይገኛል። ቀደም ሲል ትኩረት አጥቶ የነበረውን የእንስሳት ተዋጽኦ ልማት በቅንጅትና በቴክኖሎጂ በመደገፍ ረገድ በአካባቢው ተጨባጭ ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል። በግብርና ሚኒስቴር መረጃ መሠረት መርሃ ግብሩ ከመጀመሩ በፊት የነበረው 7 ነጥብ 1 ቢሊዮን ሊትር የወተት ምርት ዘንድሮ 15 ነጥብ 7 ቢሊዮን ሊትር መድረሱ፣ ቀደም ሲል በዓመት ይሰራጭ የነበረው የዶሮ ጫጩት ከ26 ሚሊዮን ወደ 184 ሚሊዮን ማደጉ እንዲሁም የእንቁላል ምርት ከ3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ወደ 11 ነጥብ 7 ቢሊዮን ከፍ ማለቱ የዚሁ አገራዊ ስኬት ማሳያዎች ናቸው።   ይህ የተጀመረው አበረታች ሂደት እንደ ወተት፣ ማር፣ ሥጋ፣ አሳ እና እንቁላል ያሉ ምርቶች የቅንጦት ሳይሆኑ የዜጎች የዕለት ተዕለት የሥርዓተ ምግብ አካል እንዲሆኑ በማስቻል ረገድም ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። በቢሾፍቱ ከተማና አካባቢዋ ለሚኖሩ በርካታ ዜጎች የአመጋገብ ሥርዓትን ከመቀየር ባለፈ፣ የኢኮኖሚ አቅማቸውን የለወጠ የሕይወት ጉዞን ፈጥሮላቸዋል። አቶ ከፈለኝ ጫላ ቀደም ሲል በመንግሥት ተቋም ተቀጥረው የሚሠሩ መደበኛ ሠራተኛ ነበሩ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ላይ ዜጎች እንዲሳተፉ ጥሪ ሲቀርብ ግን የቀደማቸው አልነበረም።   በተመቻቸላቸው የብድር አገልግሎት በመታገዝ በአንድ የወተት ላም ሥራቸውን ጀመሩ። ዛሬ ላይ ግን ታሪካቸው ሙሉ በሙሉ ተቀይሯል። የነበራቸውን ብቸኛ ላም ተንክባክበውና አርብተው በአሁኑ ወቅት የወተት ላሞቻቸውን ቁጥር 15 ማድረስ ችለዋል። "መንግሥት ያደረገልኝ ተከታታይ ድጋፍና ክትትል ለዚህ ውጤት እንድበቃ ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክቶልኛል" ይላሉ አቶ ከፈለኝ። የራሳቸውን ኑሮ ከመቀየር ባለፈ፣ የሚያመርቱትን ወተት ለአካባቢው ማኅበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ገበያውን በማረጋጋት ረገድ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛሉ። በተጨማሪም በመስኩ ለሌሎች ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ችለዋል።   ሌላኛው በዚሁ መርሃ ግብር ሕይወታቸው የተቀየረው ሥራ ፈጣሪ አቶ ጌቱ ብሩ ናቸው። እሳቸው ደግሞ በተቀናጀ የዶሮና የዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ ላይ ነው የተሰማሩት። የሌማት ትሩፋት ያመጣላቸው በረከት ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ከመጥቀም አልፎ የንግድ አድማሳቸውን አስፍቶላቸዋል። ከልማቱ በሚያገኙት የምርት ውጤት የራሳቸውን ሆቴል መክፈት የቻሉ ሲሆን፣ ለበርካታ ዜጎችም አዲስ የሥራ ዕድል ፈጥረዋል።   "ለሆቴላችን የምግብ ግብዓት የሚሆነውን ምርት የምናቀርበው ከራሳችን የዶሮና የዓሣ እርባታ ማዕከል ነው" የሚሉት አቶ ጌቱ፣ ዘርፉ ሰፊና ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት የሚቻልበት መሆኑን ይመሰክራሉ። አቶ ጌቱ እቅዳቸው እዚህ ላይ ብቻ አያበቃም፤ በቀጣይ የሌማት ትሩፋት ምርቶችን እሴት ጨምረው ለከተሞች ከማቅረብ ባለፈ ወደ ውጭ ሀገር ለመላክና ለሀገር የውጭ ምንዛሬ የማስገኘት ውጥን አላቸው። ሌሎችም በዚህ ሥራ ላይ ቢሰማሩ ከራሳቸው አልፈው ሀገርንና ወገንን መለወጥ እንደሚችሉም ነው የጠቆሙት።   በተመሳሳይ በዶሮ እርባታ ሥራ ላይ የተሰማሩት አቶ ደረጄ አበበ መርሃ ግብሩ ከፍተኛ ገቢ እንዲያገኙ እንዳስቻላቸው ይናገራሉ። የዶሮ እንቁላል ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለአካባቢው ማኅበረሰብ በስፋት በማቅረብ የኑሮ ውድነቱን ለመቋቋም የበኩላቸውን እየተወጡ ይገኛሉ። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር)፥ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በርካታ ስኬቶች የተመዘገቡበትና የዜጎችን የምግብና ሥርዓተ ምግብ አቅም እያሳደገ የሚገኝ ኢኒሼቲቭ ነው ብለዋል።   ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ሀገራዊ ጥረት ለማሳካት የእንስሳት ሀብት ልማት ዘርፍ ያለው ሚና ከፍተኛ መሆኑንም ጠቅሰዋል። አክለውም፤ ኢኒሼቲቩ በቤተሰብ ደረጃ የዶሮ እርባታን ባህል እንዲሆን በማድረግ፣ በተለይም ሕፃናትና እናቶች የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ በማስቻል ረገድ መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑንና ምርቶችን በስፋት ለገበያ እንዲቀርቡ በማስቻል ረገድ ትርጉም ያለው ውጤት ማምጣቱን ገልጸዋል።    
በጎንደር ከተማ ወደ 49 ሺህ ለሚጠጉ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል ተፈጥሯል
Jul 10, 2026 504
ጎንደር፤ ሃምሌ 3/2018 (ኢዜአ)፡- በጎንደር ከተማ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 49 ሺህ ለሚጠጉ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል መፍጠር መቻሉን የከተማ አስተዳደሩ የስራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የከተማ አስተዳደሩ ሥራና ክህሎት መምሪያ ያለፈውን በጀት ዓመት የሥራ አፈፃፀም ግምገማና የ2019 ዓ.ም ዕቅድ ትውውቅ መድረክ ዛሬ በጎንደር ከተማ አካሄዷል።   የመምሪያው ኃላፊ አቶ አበበ ላቀው በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በከተማዋ በተካሄዱ የኢንዱስትሪ፣ የከተማ ግብርና፣ የንግድና አገልግሎት ዘርፎች ለወጣቱ የሥራ ዕድል ለመፍጠር በትኩረት ተሰርቷል። በዚህም በበጀት ዓመቱ ለ44 ሺህ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ በተደረገ ጥረት፣ ከ48 ሺህ 900 በላይ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ከዕቅድ በላይ መፈጸም መቻሉን ገልፀዋል። ከዕቅድ በላይ ማስመዝገብ የተቻለውም በተገኘው ሰላም ባለሀብቱ ተረጋግቶ ወደ ልማት በመግባቱና አመራሩና ባለሙያው የተጠናከረ ድጋፍ በማድረጋቸው መሆኑንም አብራርተዋል። ከአበዳሪ ተቋማት ጋር በመተባበርም ለ2 ሺህ 689 ኢንተርፕራይዞች 665 ሚሊዮን ብር ብድር በማሰራጨት ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። የሥራ ዕድሉን መፍጠር የተቻለውም በኮንስትራክሽን፣ በከተማ ግብርና፣ በአነስተኛ ንግድና ሌሎች የሥራ ዘርፎች መሆኑን አስረድተዋል። በተጨማሪም መምሪያው ከሥራ ዕድል ፈጠራ ጎን ለጎንም ለ856 ኢንተርፕራይዞች የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን ድጋፍ በማድረግ ያሉባቸውን ችግሮች ለመፍታት ጥረት ማደረጉን ገልጸዋል። ከጎንደር ከተማ አስተዳደር መሬት መምሪያ ጋር በመተባበር በኮሪደር ልማት ለተነሱ 334 ግለሰቦች የመስሪያና የመሸጫ አገልግሎት መስጫ ሼድ በማስገንባት ማስረከብ መቻሉንም አክለዋል።   በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የጎንደር ከተማ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኃላፊ አቶ ግርማይ ልጅዓለም በበኩላቸው፤ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በሥራ ዕድል ፈጠራ አበረታች ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። ይህም የከተማው አስተዳደር የወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራ ስራን በዋነኝነት ይዞ በየጊዜው እየገመገመና የቀጣይ አቅጣጫ በማስቀመጥ በመስራቱ የመጣ ውጤት መሆኑን አስረድተዋል።    
የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የተወሰደው አማራጭ ገበያን የማስፋት ሥራ ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው
Jul 10, 2026 750
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2018(ኢዜአ)፦የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የተወሰደው አማራጭ ገበያን የማስፋት ሥራ ተጨባጭ ውጤት እያመጣ መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልሃኪም ሙሉ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በሰጡት ማብራሪያ መንግሥት የኑሮ ውድነትንና ገበያን ለማረጋጋት በርካታ እርምጃዎችን እየወሰደ ይገኛል ብለዋል።   ከተወሰዱ ቀዳሚ እርምጃዎች መካከል የሸማቾችን አማራጭ ማሳደግ አንዱ ሲሆን፣ በዚህም የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ተደራሽነት ከ2 ሺህ በላይ ማድረስ መቻሉን አስታውቀዋል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልሃኪም ሙሉ (ዶ/ር) እንደገለፁት፤ የዋጋ ግሽበትን ወደ ነጠላ አሃዝ ለማውረድ በርካታ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቁመዋል። ለዚህም በንግድ ሥርዓቱ ላይ የሚስተዋሉ ህገወጥ ተግባራትን መከላከልና መቆጣጠር፣ የምርት አቅርቦትን ማሳደግና አማራጭ ገበያን ማስፋት ላይ ትኩረት መደረጉን ነው ያብራሩት።   በተለይም በንግድ የእሴት ሰንሰለት ውስጥ የህገወጥ አካላትንና የደላሎችን ጣልቃ ገብነት በማስቀረት ሸማቹንና አምራቹን በቀጥታ የሚያገናኙ የገበያ ማዕከላትን በማደራጀት ረገድ አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ አዳዲስ የገበያ አማራጮችን ለመፍጠር በተደረገው ጥረት በበጀት ዓመቱ 804 አዳዲስ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች መከፈታቸውን ጠቅሰው፥ በአጠቃላይ 2 ሺህ 369 መድረሳቸውን ገልጸዋል። እነዚህ ማዕከላት ያለምንም የደላላ ጣልቃ ገብነት ቀጥተኛ ሸመታ የሚከናወንባቸው በመሆናቸው በተለይ መካከለኛና ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን የማህበረሰብ ክፍሎች በእጅጉ መደገፍ መቻላቸውን ነው ያነሱት። ከዋጋ አኳያም ከመደበኛው ገበያ ጋር ሲነጻጸር ከ15 በመቶ እስከ 30 በመቶ የሚደርስ ቅናሽ ያላቸው መሆኑ ተናግረዋል።   በማዕከላቱ በኩል በግብርና እና በኢንዱስትሪ ምርቶች ላይ ሰፊ የገበያ ትስስር የተፈጠረ ሲሆን በዚህም በስፋት አትክልትና ፍራፍሬ፣ የሰብል ምርቶች እና የኢንዱስትሪ ምርቶች እየቀረቡ ነው ብለዋል። እንደሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ ከቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በተጨማሪ የገበያ ትስስሩን ይበልጥ ለማዘመን የሁለተኛ ደረጃ የገበያ ማዕከላትን የመገንባት ስራ በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። ይህንን ዘመናዊ አሠራር በስፋት በመተግበር ረገድ አዲስ አበባ ከተማ፣ የኦሮሚያ ክልል እና የአማራ ክልል ግንባር ቀደም ተጠቃሽ መሆናቸውን በመጥቀስ፥ ወደ ሌሎች ክልሎችም ተሞክሮው እየተስፋፋ ነው ብለዋል።   እነዚህ ሁለተኛ ደረጃ የግብይት ማዕከላት የግብይት ሰንሰለቱን በማሳጠር ለገበያ መረጋጋት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙም አስገንዝበዋል።      
የመስኖ ልማት ሲገጥመን የነበረውን የመኖ እጥረት ችግር ቀርፎልናል -የዳሰነች ወረዳ አርብቶ አደሮች
Jul 10, 2026 425
ጂንካ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):-በመስኖ ታግዘው የጀመሩት የእንስሳት መኖ ልማት ሲገጥማቸው የነበረውን የመኖ እጥረት ችግር እንደቀረፈላቸው በደቡብ ኦሞ ዞን የዳሰነች ወረዳ አርብቶ አደሮች ገለጹ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደቡብ ኦሞ ዞን የዳሰነች ወረዳ አርብቶ አደሮች መስኖን ተጠቅመው እያለሙት ባለው የተሻሻለ የእንስሳት መኖ ከዚህ ቀደም ሲያጋጥጥም የነበረው የመኖ እጥረት እየተፈታ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የቦርኮኖች ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ናማዴ አርዴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል በአካባቢው በሚከሰት ድርቅ የእንስሳት መኖ እጥረት ያጋጥም ነበር።   እጥረቱ በሚከሰትበት ወቅት መንግስት መኖ ከሌላ አካባቢ በማምጣት ድጋፍ ያደርግ እንደነበር ጠቅሰው ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት በአካባቢያችን መኖ እንድናለማ ተደርጓል ብለዋል። በመስኖ ታግዘው በ5 ሄክታር ኩታ ገጠም መሬት ላይ የጀመሩት የእንስሳት መኖ ልማት የመኖ ችግራቸውን ከመፍታት ባለፈ ከመኖ ሽያጭ ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኙ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል ። ከዚህ ቀደም በአካባቢው ድርቅ በተከሰተበት ወቅት የግጦሽ ሣር ፍለጋ ሲንቀሳቀሱ አላስፈላጊ እንግልት ይገጥማቸው እንደነበር ያስታወሱት ደግሞ በወረዳው የራቴ ቀበሌ ነዋሪ ፔሬ ሎኮሮም ናቸው።   አሁን ላይ በመንግሥት ድጋፍ በመስኖ በመታገዝ በአካባቢው መኖ ማልማት በመጀመራቸው ችግሩ እንደተቀረፈ ገልፀው የመኖ ልማቱ ለከብቶቻቸው ዋስትና መሆኑን ተናግረዋል። የዳሰነች ወረዳ ግብርና ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍቅረማርያም አይመላ፤ የአርብቶ አደሮችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ሰፋፊ የግብርና ልማት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   ከሰብል ምርት ባሻገር አርብቶ አደሮች በአካባቢያቸው ከፍተኛ የፕሮቲን ይዘት ያላቸውን የመኖ ዝርያዎች በማልማትና እንስሳትን በመመገብ የተሻለ ጥቅም እንዲያገኙ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። አርብቶ አደሩ ጥራትን መሰረት ያደረገ የእንስሳት እርባታ ዘዴን እንዲከተል በማድረግ የእንስሳት እርባታውን ለማዘመን ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ የቆላማ አካባቢ ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት፣ የእንስሳት ሃብት ልማት ባለሙያ ዶክተር ይብራህ ገብረመስቀል በበኩላቸው፤ በክልሉ ቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አማካኝነት በወረዳው ሁለት ቀበሌዎች በሙከራ ደረጃ የተሻለ የመኖ ዝርያ የማስተዋወቅ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።   ዝርያው ድርቅን መቋቋም የሚችልና ከፍተኛ የፕሮቲን ይዘት ያለው መሆኑን ጠቅሰዋል። በመኩራ ደረጃ በሁለት ቀበሌዎች በ10 ሄክታር መሬት ላይ እየለማ ያለው የመኖ ዝርያው ውጤታማ መሆኑን አንስተው፥ በቀጣይም በሌሎች ወረዳዎች ተሞክሮውን ለማስፋት ይሰራል ብለዋል።
በክልሉ ለመስኖ ልማት የተሰጠው ትኩረት በድርቅ ተጠቂ የነበሩ አከባቢዎችን ወደ አምራችነት አሸጋግሯል  
Jul 10, 2026 439
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):-በኦሮሚያ ክልል ለመስኖ ልማት የተሰጠው ትኩረት በድርቅ ተጠቂ የነበሩ አከባቢዎችን ወደ አምራችነት ማሸጋገሩን የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ በሪሶ ፈይሳ ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት የሥራ አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም ዘንድሮ በኩታ ገጠም፣ በመስኖና በቴክኖሎጂ ታግዞ በለማ 29 ሚሊዮን ሄክታር መሬት 1 ነጥብ 3 ቢሊዮን ኩንታል ምርት መገኘቱን ገልጸዋል፡፡ ቀደም ሲል በድርቅ ይፈተን የነበረው የቦረና አካባቢ በአሁኑ ወቅት በስንዴ ልማት ያሳየውን ስኬት በዋነኛ ማሳያነት አንስተዋል። የኦሮሚያ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ የሆኑት አቶ በሪሶ ፈይሳ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ በክልሉ የተዘረጉ ዘመናዊ አሠራሮች፣ የተሳለጠ የግብዓት አቅርቦት እና የቴክኖሎጂ ሽግግር የግብርናውን ዘርፍ ወደ አዲስ ምዕራፍ እንዳሸጋገሩት ገልጸዋል።   ባለፉት ዓመታት በባህላዊ መሣሪያዎች ላይ ብቻ ተደግፎ የነበረውን ግብርና ወደ መካናይዜሽን እየተሸጋገረ መሆኑ ትልቅ እምርታ ያመጣ ስትራቴጂካዊ እርምጃ መሆኑን ጠቁመዋል። የመካናይዜሽን መስፋፋት አርሶ አደሩን ከዕለታዊ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ የሚሆን ምርት በስፋት እንዲያመርትና ወደ ላቀ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት እንዲሸጋገር በር ከፍቶለታል ብለዋል። በክልሉ በስፋት ተግባራዊ የተደረገው የኩታ ገጠም የእርሻ ሥርዓት፣ ይፋ የተደረጉ ግብዓቶችና የመካናይዜሽን ቴክኖሎጂዎችን በአንድ ቋት ውስጥ በጥምረት ለመጠቀም ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል። በክልሉ በስፋት የተተገበረው የኩታ ገጠም የስንዴ ልማት በበጋ መስኖ፣ በመኸር እና በበልግ ወቅቶች በተከናወኑ የተቀናጁ የልማት ሥራዎች፤ ከ6 ነጥብ 8 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከ3 መቶ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ማምረት መቻሉን ጠቁመዋል፡፡ ይህ ውጤት የክልሉ ግብርና እየተመራበት ያለው አዲስ አቅጣጫ ውጤታማና ተስፋ ሰጪ ለመሆኑ ትልቅ ማሳያ ነው ሲሉ ገልጸዋል።   ቀደም ሲል በከፍተኛ ድርቅ ይታወቁ የነበሩ ቆላማ አካባቢዎችን ቀጣይነት ወዳለው አምራችነት ለመቀየር የተከናወኑት ተግባራት የዘርፉ ትልቅ ስኬቶች ናቸው ብለዋል። በተለይም በቦረና ዞን ወደ ሥራ የገቡት የፊና መስኖ ግድብና መሰል ፕሮጀክቶች የማኅበረሰቡን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በተግባር አረጋግጠዋል ብለዋል። የመስኖ ፕሮጀክቶቹ አርብቶ አደሩ ማኅበረሰብ ለዘመናት ለውኃና ለሳር ፍለጋ ከቦታ ወደ ቦታ ያደርግ የነበረውን ስደትና ባህላዊ የሕይወት ዘይቤ ከመሠረቱ መለወጣቸውንም ጠቅሰዋል፡፡ እነዚህ ስትራቴጂካዊ ሥራዎች በአካባቢው ላይ የነበረውን እይታ በመቀየር፣ ዛሬ ላይ ቆላማ አካባቢዎች የሰፊ የስንዴ ልማትና የመስኖ ማዕከል እንዲሆኑ ማስቻሉንም ጠቁመዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ተግባራዊ የተደረገው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በክልሉ ባሉ ዞኖች፣ ወረዳዎችና ቀበሌዎች ሁሉ በስፋትና በተቀናጀ ሁኔታ እየተተገበረ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ በሥርዓተ-ምግብና በኢኮኖሚው ዘርፍ ተጨባጭ ለውጥ በማምጣት ላይ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም በዶሮ ሥጋ፣ በእንቁላል፣ በወተትና በማር ምርት ከፍተኛ እምረታ መምጣቱን ጠቅሰው የተሻሻሉ የወተት ላሞች ዝርያ አቅርቦት እና የመኖ ልማት ሥራዎች በትይዩ በመከናወናቸው የወተት ምርት በከፍተኛ መጠን መጨመሩን ጠቁመዋል፡፡ ይህ ስኬት የአርሶ አደሩ የገቢ ምንጭ እንዲሰፋና ጤናማ ማኅበረሰብ እንዲገነባ ትልቅ አቅም መሆኑንም ጠቁመው መርሐ ግብሩ ገበያን ከማረጋጋት ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የሥራ እድል መፍጠር መቻሉንም አብራርተዋል፡፡
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የጌዴኦን ባህላዊ መልክዓ ምድር ከጎበኙ ቱሪስቶች 50 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ ተገኝቷል
Jul 10, 2026 357
ዲላ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የጌዴኦን ባህላዊ መልክዓ ምድር ከጎበኙ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶች 50 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ መገኘቱን የዞኑ ቱሪዝም መምሪያ ገለጸ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ እድሉ ታደሰ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የዞኑን የቱሪዝም አቅም አሟጦ ለመጠቀም የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ደረጃና አገልግሎት በማሻሻል ለጎብኝዎች ምቹ ሁኔታ መፍጠር ተችሏል።   የጌዲኦ ባህላዊ መልክዓ ምድር ያቀፋቸውን ተፈጥሯዊ፣ ባህላዊና ታሪካዊ መስህቦችን በማልማትና በማስተዋወቅ ቱሪስት መሳብ የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውንም ገልጸዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት መልክዓ ምድሩ ከ40 ሺህ በሚበልጡ የውጭና የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች መጎብኘቱን ጠቅሰው፣ 50 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢም መገኘቱን አስታውቀዋል። ገቢው ካለፉት ዓመታት ብልጫ ያለው ሲሆን የቡና ቱሪዝም መስፋፋት፣ የምርምር ስራዎች መጠናከር እንዲሁም በአካባቢው ያለው ሰላም ለገቢው መጨመር ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። በዞኑ የመዳረሻ ስፍራዎች ልማትን በማጠናከር የዘርፉን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊው፤ በኮቾሬ ወረዳ የሚገኘውን የራኮ ተራራ ለጎብኚዎች ምቹ የማድረግ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። የራኮ ተራራን ውብ ገጽታ በማልማትና በማስተዋወቅ ቱሪስቶችን ለመሳብ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የኮቾሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ዳዊት ጀቦ (ዶ/ር) ናቸው።   በተለይም ወደ ተራራው መውጫ መንገድና በተራራው ላይ መቆያ ስፍራ፣ እንዲሁም ሕብረተሰቡን ያሳተፈ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች መከናወናቸውን አንስተዋል። ይህም የተራራውን የተፈጥሮ አደጋ ተጋላጭነት በመቀነስ ለመስህብነቱ ያለው አቅም እንዲጎለበት እያገዘ መሆኑን አስረድተዋል። የዳራሮ "ሀገርህን እወቅ" ማኅበር ሰብሳቢ መላኩ ታደሰ በበኩላቸው፤ “ሀገርን ማወቅ አካባቢን ከማወቅ ይጀምራል” በሚል መሪ ሐሳብ የጌዴኦ ባህላዊ መልክዓ ምድርን የማወቅና የማስተዋወቅ ሥራዎችን እያከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዚህም የመስህብ ስፍራዎችን በመጎብኘትና በተለያዩ አማራጮች በማስተዋወቅ ቱሪስቶች በስፋት ወደ አካባቢው እንዲመጡ ከመስራት ባለፈ፣ ለጎብኚዎች መረጃ በመስጠት የዘርፉን ተጠቃሚነት ለማጎልበት እየሰሩ እንደሚገኙም ተናግረዋል።
የአማራ ልማት ማህበር/አልማ/ የህዝብን ጥያቄ መሰረት ያደረጉ የልማት ስራዎችን እያከናወነ ነው
Jul 10, 2026 228
ባህር ዳር ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- የአማራ ልማት ማህበር (አልማ) የህዝብን ጥያቄ መሰረት ያደረጉ ውጤታማ የልማት ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ አስታወቀ። ማህበሩ ከሐምሌ 1 እስከ ሐምሌ 15 ቀን 2018 ዓ.ም የሚካሄደውን የአልማ ሳምንትና የ35ኛ ዓመት የምስረታ በዓል አከባበር በተመለከተ መግለጫ ሰጥቷል። የማሕበሩ ምክትል ስራ አስፈፃሚ አቶ አበረ መኩሪያ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ አልማ የልማት ፍላጎቶችን በመለየት ውጤታማ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል። በተለይም በትምህርት፣ በጤና ፣ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ በአደጋ ጊዜ ምላሽ በመስጠት እና መልሶ ማቋቋም ስራዎች ላይ ተሳትፎ እያደረገ እንደሚገኝም ነው የገለጹት። ማህበሩ ከ2017 እስከ 2021 የሚቆይ ስትራቴጂክ እቅድን ተግባራዊ በማድረግ 3 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ሀብት ማሰባሰብ መቻሉን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም 23 ነጥብ 9 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን በመፈራረም እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም አንድ ሺህ 658 የመማሪያ ክፍሎችን በመገንባት ለአገልግሎት ያበቃ ሲሆን በርካታ የመማሪያ ክፍሎችንም እየተገነቡ መሆኑን ጠቅሰዋል። በጤናው ዘርፍም 55 የጤና ኬላዎች ፣ ጤና ጣቢያ እና የህዝብ መድሃኒት ቤቶችን በመገንባት ለአገልግሎት እንዲበቁ ማድረጉን አንስተዋል። ለስራ እድል ፈጠራ የሚያገለግሉ የመስሪያና የመሸጫ ሼዶችን ገንብቶ ከማስረከብም ባለፈ ለወጣቶች የህይወት ክህሎት ስልጠና በመስጠት ዘርፉን የማጠናከር ስራ መሰራቱን አብራርተዋል። ማህበሩ በቀጣዩ በጀት ዓመትም የአባላቱን ቁጥር አሁን ካለበት 4 ነጥብ 9 ሚሊዮን ወደ 5 ነጥብ 9 ሚለዮን በማሳደግና ሀብት በማሰባሰብ የልማት ስራዎችን ለማከናወን ማቀዱን አብራርተዋል። ከሐምሌ 1 ቀን እስከ ሐምሌ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ለ7ተኛ ጊዜ የሚከበረው የአልማ ሳምንት ከ35ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉ ጋር ተቀናጅቶ እየተከበረ ይገኛል ብለዋል። ይህ በየደረጃው የሚከበረው የአልማ ሳምንት የህዝብ ንቅናቄ ለመፍጠር፣ አዳዲስ አባላትን ለማፍራትና ለልማት ስራዎች የሚውል ሃብት ለማሰባሰብ ዓላማ የደረገ ነው ብለዋል። መርሐግብሩ በጎዳና ላይ ሩጫ፣ በፕሮጀክቶች ምረቃ፣ በችግኝ ተከላ፣ በፓናል ውይይት፣ በፎቶ ኤግዚቢሽንና የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራ በመስራት ይከበራል። አልማ እያከናወናቸው የሚገኙ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተግባራትን በማጠናከር የህዝብ የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ አባላትና ደጋፊዎች ከመቼውም ጊዜ በላቀ ድጋፍና እገዛቸውን እንዲያጠናክሩ ጥሪ አቅርበዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በተያዘው መኸር ከ48 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቢራ ገብስ እየለማ ነው
Jul 10, 2026 184
አምቦ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- በምዕራብ ሸዋ ዞን በተያዘው መኸር ከ48 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቢራ ገብስ እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። በጽሕፈት ቤቱ የአዝዕርት ልማት ባለሙያ አቶ ደጀኔ ደቡሼ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ለቢራ ገብስ ልማት ተስማሚ የሆኑ ወረዳዎች ተለይተው መሬቱን በዘር የመሸፈን ስራ በተጠናከረ ሁኔታ እየተከናወነ ይገኛል።   ይህም የሀገር ውስጥ የኢንዱስትሪ ግብዓትን በበቂ ሁኔታ ለመተካትና የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ በተያዘው መኸር በ48 ሺህ 465 ሄክታር መሬት ላይ የቢራ ገብስ እየለማ መሆኑን ገልጸው ለስኬታማነቱም በየደረጃው የሚገኙ የግብርና ባለሙያዎችና አጋር አካላት በቅንጅት አርሶ አደሩን በቅርበት እያገዙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግም የተሻሻሉ የቢራ ገብስ ዝርያዎችን እና የግብርና ግብዓትን ለአርሶ አደሮች ማቅረብን ጨምሮ፣ ማሳዎችን በኩታ ገጠም የማደራጀት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን አስታውሰዋል። በተለይም በአምቦ፣ አዳ በርጋ፣ ጅባት፣ ጀልዱ፣ ድሬ እንጪኒ፣ ኤጄሬ እና ኤጀርሳ ለፎ ወረዳዎች የቢራ ገብስ ልማት ስራው በስፋት ከሚከናወንባቸው አካባቢዎች መካከል በዋናነት ተጠቃሽ መሆናቸውን አንስተዋል። እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴ ከሁለት ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ታርሶና ለስልሶ በዘር የተሸፈነ ሲሆን፣ በዚህ የልማት ስራ ላይም 5 ሺህ 520 አርሶ አደሮች እየተሳተፉ ይገኛሉ ብለዋል። በምርት ዘመኑ ከሚለማው መሬት በአጠቃላይ ከ1 ሚሊዮን 796 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ርብርብ እየተደረገ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። የዘንድሮው የገብስ ልማት ስራ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር በ465 ሄክታር መሬት ብልጫ እንዳለውም ጠቁመዋል።   በዞኑ የአምቦ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ገላና ሰቦቃ በሰጡት አስተያየት፤ በዘንድሮው አዝመራ አንድ ሄክታር ማሳቸውን በቢራ ገብስ ዘር መሸፈናቸውን ተናግረዋል። የተሻለ ምርት ለማግኘትም ምርጥ ዘርና የምርት ማሳደጊያ ማዳበሪያ በመጠቀምና በግብርና ባለሙያ በሚሰጣቸው ምክረ ሐሳብ በመታገዝ የግብርና ስራቸውን እያከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል።   የዚሁ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ሌላኛው አርሶ አደር ብርሃኑ ተሾመ በበኩላቸው፤ በቢራ ገብስ ልማት ሥራ ላይ መሳተፍ ከጀመሩ ሰባት ዓመታትን እንዳሳለፉ ገልጸዋል። በዚህ ዓመትም በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ ታግዘው የተሻለ ምርት ለማግኘትና ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን ተግተው እየሰሩ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
በዞኑ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በስፋት ለማምረት ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 10, 2026 243
አዳማ ፤ ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):- በምስራቅ ሸዋ ዞን የግብርናውን ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉና ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በስፋት ለማምረት ትኩረት መሰጠቱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለፀ። የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለ2018/19 ዓ.ም የምርት ዘመን ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ የጥራጥሬና የብርዕ ሰብሎችን ለማምረት በትኩረት እየተሰራ ነው። የግብርናውን ምርታማነት ለማሳደግም ለግብዓት አቅርቦት፣ ለግብርና ቴክኖሎጂ እንዲሁም ለባለሙያ ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠሉን አስረድተዋል።   ይህም የዞኑን የግብርና ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በስፋት ለማምረት እያገዘ መሆኑን ገልጸዋል። ወደ ውጭ ከሚላኩ ምርቶች መካከልም ቦሎቄና ሽንብራን በኩታ ገጠም በማልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ልዩ ትኩረት መሰጠቱን አስረድተዋል። ባለፈው የበጀት ዓመት 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ቦሎቄ መገኘቱን የገለጹት አቶ አብነት፤ ከተመረተው ምርት ውስጥ 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታሉ ለውጭ ገበያ መቅረቡን ጠቁመዋል። በዘንድሮው የመኸር ወቅት ተግባሩን ይበልጥ በማስቀጠል፣ ከ80 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም በቦሎቄ በማልማት ከ2 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት መታቀዱን አስታውቀዋል።   ከዚህ አኳያ ሽንብራና ሌሎች የጥራጥሬ ሰብሎችን በ12 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ በማልማት ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለውጭ ገበያ ለማቅረብ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በተጨማሪም የጥጥ ልማትን በሙከራ ደረጃ በመተግበር ለኢንዱስትሪዎች ግብዓት ለማዋል፣ እንዲሁም የአርሶ አደሩንና የአርብቶ አደሩን ገቢ ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም