ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያና ዩናይትድ ኪንግደም ታሪካዊ ግንኙነት ወደላቀ ስትራቴጂክ አጋርነት እየተሸጋገረ ነው 
Jun 25, 2026 577
አዲስ አበባ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያና ዩናይትድ ኪንግደም ታሪካዊ ግንኙነት ወደላቀ ስትራቴጂክ የዲፕሎማሲ አጋርነት እየተሸጋገረ መሆኑን በዩናይትድ ኪንግደም የኢትዮጵያ አምባሳደር ብሩክ መኮንን ገለጹ። በኢትዮጵያ እና እንግሊዝ መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ትብብር ለማሳደግ የተዘጋጀው የኢትዮ-እንግሊዝ የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረም 2026 በለንደን ከተማ ተካሂዷል።   በዩናይትድ-ኪንግደም የኢትዮጵያ አምባሳደር ብሩክ መኮንን በዚሁ ጊዜ፤ ኢትዮጵያና እንግሊዝ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ዘመናትን የተሻገር ታሪካዊ ግንኙነት ያላቸው ወዳጅ ሀገራት ናቸው ብለዋል። የሀገራቱ መልካም ግንኙነትም የንግድና ኢንቨስትመንት የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ትብብርን በማሳደግ የህዝብ ለህዝብ ትስስርን ጭምር እያጠናከረ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅትም የኢትዮጵያና ዩናይትድ ኪንግደም ታሪካዊ ግንኙነት ወደላቀ ስትራቴጂክ የዲፕሎማሲ አጋርነት እየተሸጋገረ መሆኑን ተናግረዋል። የሀገራቱ የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረምም የኢኮኖሚክ ዲፕሎማሲ አጋርነትን ለማጎልበት ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የብዝኅ ዘርፍ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ ለሀገራቱ ሁለንተናዊ የዲፕሎማሲ ትብብር አስቻይ ሁኔታ መፍጠሩንም አንስተዋል። በቀጣይም የሀገራቱን ሁለንተናዊ የዲፕሎማሲ ትብብር የበለጠ በማጠናከር የጋራ ተጠቃሚነትን ለማሻሻል በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በዩናይትድ ኪንግደም የኢትዮጵያ ኤምባሲም የሁለቱን ሀገራት የንግድ፣ የኢንቨስትመንትን፣ የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ትብብር ወደ ላቀ ስትራቴጂክ አጋርነት ለማሸጋገር በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በፎረሙ ላይ የሀገራቱ የፖሊሲ አውጪ ሙያተኞች፣ ባለሃብቶችና የተለያዩ ተቋማት ጋር የሃሳብ ልውውጦች መደረጋቸው ተመላክቷል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች የሚመልሱ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቁ
Jun 25, 2026 435
አምቦ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን የቆዩ የልማት ጥያቄዎች ለመፍታት የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት አውታሮች በሁለት ዙር ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በዞኑ ኢሉ ገላን ወረዳ ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁት ኮሪደር ልማት፣ የእንስሳት ጤና ኬላ፣ የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት እና ሌሎች የመሰረተ ልማት ተቋማትም ይገኙበታል። በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የምዕራብ ሸዋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ እንደገለጹት፤ በዞኑ በሕዝብና በመንግሥት ትብብር የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት እየበቁ ነው።   በበጀት ዓመቱ በመጀመሪያው ዙር 391 የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው አገልግሎት መጀመራቸውን የገለጹት አስተዳዳሪው፤ የሁለተኛው ዙር ምረቃ በኢሉ ገላን ወረዳ መጀመሩን ጠቁመዋል። ግንባታቸው ተጠናቆ ምርቃታቸው የተጀመረው የሁለተኛ ዙር ፕሮጀክቶች ቁጥር 128 መሆኑንም ገልጸዋል። የኢሉ ገላን ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አሚን ነሻ በበኩላቸው፤ በወረዳው በመንግሥት በጀትና በሕብረተሰቡ ተሳትፎ ከ106 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 18 የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን አስታውቀዋል።   የተገነቡት መሰረተ ልማቶች የአካባቢውን ሕብረተሰብ ዘመናት ያስቆጠሩ ጥያቄዎች የሚፈቱ መሆናቸውን የገለጹት የወረዳው አስተዳዳሪ፤ ሕዝቡ ለፕሮጀክቶቹ አስፈላጊውን እንክብካቤ በማድረግ ለመጪው ትውልድ ማስተላለፍ እንዳለበት አሳስበዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢሉ ገላን ወረዳ ነዋሪዎችም በአካባቢያቸው ለአገልግሎት የበቁ ፕሮጀክቶች የረጅም ጊዜ ጥያቄያቸውን ከመመለስ ባለፈ፣ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያሳድጉት ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።   አቶ ሁንዱማ ታረሳ "በቀበሌያችን የተገነባው ዲጂታል ቤተ መጻሕፍት አገልግሎት መጀመሩ የአካባቢው ተማሪዎች በቴክኖሎጂ ታግዘው ዕውቀት እንዲቀስሙና በሀገር አቀፍም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ትልቅ እገዛ ያደርጋል" ብለዋል።   ወጣት ደራርቱ ወጋሪ በበኩሏ፤ ለአገልግሎት የበቁት መሰረተ ልማቶች የአካባቢውን ሕብረተሰብ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ከመሆናቸውም በላይ፣ ለወጣቶች ሰፊ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ በመሆናቸው ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ገልጻለች።
የሀረር ፌዴራል ፖሊስ ሆስፒታል ማስፋፊያ የክልሉን የሜዲካል ቱሪዝም የሚያጎለብት ነው
Jun 25, 2026 240
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 18/2018/(ኢዜአ) ፦ የሀረር ፌዴራል ፖሊስ ሆስፒታል ማስፋፊያ ፕሮጀክት የክልሉን የሜዲካል ቱሪዝም ይበልጥ የሚያጎለብት ነው ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ገለፁ። ርዕሰ መስተዳድሩ የሀረር ፌዴራል ፖሊስ ሆስፒታል ማስፋፊያ የግንባታን የአፈጻጸም ሂደት ተመልክተዋል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በጉብኝታቸው የሪፈራል ሆስፒታሉን ግንባታ በተያዘለት የጊዜ ገደብ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ስለመሆኑ ማየታቸውን ገልጸዋል። የሆስፒታሉ ማስፋፊያ ግንባታ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ሲጀምርም የህክምና አገልግሎቱን ወደ ተሻለ ደረጃ የሚያደርስ መሆኑን ነው የተናገሩት። በክልሉ ለጤና አገልግሎት ተደራሽነት ልዩ ትኩረት ተሰቶት ወደ ስራ መገባቱን የጠቆሙት ርዕሰ መስተዳድሩ የሆስፒታሉ ማስፋፊያም በክልሉ በጤና ዘርፍ የሚሰጠውን አገልግሎት ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የራሱን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ገልፀዋል።   በተለይ ሀረር ጎረቤት አገራትን ጨምሮ ከአጎራባች ክልሎች ለህክምና የሚመጡ በርካታ ተገልጋዮች የሚስተናገዱባት የሜዲካል ቱሪዝም ከተማ መሆኗን ጠቅሰው የሆስፒታሉ ማስፋፊያ የሜዲካል ቱሪዝሙን ይበልጥ የሚያጎለብት ነው ብለዋል። የማስፋፊያ ፕሮጀክቱ ጥሩ በሚባል አፈፃፀም ላይ እንደሚገኝ በማመላከት በፍጥነት ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት እንዲችል የክልሉ መንግስት ድጋፍ እንደሚያደርግም ርዕሰ መስተዳድሩ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ እመርታ ለውጭ አልሚ ባለሃብቶች ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳርን ፈጥሯል
Jun 25, 2026 229
አዲስ አበባ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ልማት እመርታ ለውጭ አልሚ ባለሃብቶች ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳር መፍጠሩን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ ገለጹ። በኢትዮጵያ እና ዩናይትድ ኪንግደም መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ትብብርን ለማሳደግ የተዘጋጀው የኢትዮ-እንግሊዝ የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረም 2026 በለንደን ከተማ ተካሂዷል።   የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ አምራች የሰው ኃይል፣በዓመት ከሶስት ጊዜ በላይ የሚያመርት መሬትና የብዝኅ ጸጋ ምድር ናት ብለዋል። በሀገራዊ ለውጡ ማግስት ተግባራዊ የተደረገው የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ የልማት አቅጣጫም በግብርና፣ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ቱሪዝምና ዲጂታል ኢኮኖሚ ዘርፎች ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚም በሁሉም ወቅቶች ዘመናዊ አስተራረስ ምኅዳርን በማስፋት የኢንዱስትሪ ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የኢትዮጵያን የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢ ለማሻሻል ተግባራዊ የሆኑ የሕግና የአሰራር ማሻሻያዎችም ለውጭ ባለኃብቶች አስቻይ ምኅዳር መፍጠሩን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የግብርና ምርታማነት አቅም የምግብ ሉዓላዊነትን በሚያረጋግጥ ትክክለኛ አቅጣጫ ላይ እየተመራ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል። የእንግሊዝ አልሚ ባለሃብቶችም የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ አስቻይ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳር መጠቀም የሚችሉበት ዕድል መፈጠሩንም አብራርተዋል።
የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው የተረጋጋ፣ተገማችና ተወዳዳሪ የንግድና ኢንቨስትመንት ሥነ ምህዳር ፈጥሯል
Jun 25, 2026 428
አዲስ አበባ፤ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው የተረጋጋ፣ ተገማችና ተወዳዳሪ የንግድና ኢንቨስትመንት ሥነ ምህዳር መፍጠሩን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያና እንግሊዝ መካከል ያለውን ሁሉን አቀፍ ትብብር ይበልጥ ለማሳደግ የተዘጋጀው የ“እንግሊዝ-ኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት ፎረም 2026” በለንደን ተካሂዷል። በፎረሙ ላይ የተገኙት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ምንዛሪ ግኝትን በማሳደግ ረገድ ተስፋ ሰጭ ውጤት ያስመዘገበ ሲሆን፣የተረጋጋ፣ ተገማችና ተወዳዳሪ የንግድና ኢንቨስትመንት ሥነ ምህዳር መፍጠር ችሏል። ኢትዮጵያና እንግሊዝ ከረጅም ጊዜ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ባሻገር ጥልቅና ሁሉን አቀፍ የትብብር ታሪክ ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅትም በንግድ፣በልማት አጋርነት፣ በኢንቨስትመንት መስፋፋት እንዲሁም በማደግ ላይ ባለው የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ አማካኝነት የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ይበልጥ እየተጠናከረ መምጣቱን ገልጸዋል።   ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ወሳኝ በሆነ የኢኮኖሚ ሽግግር ምዕራፍ ላይ እንደምትገኝ የጠቆሙት ሚኒስትሩ፥የዚህ ሽግግር ስኬት እውን ሊሆን የሚችለው በጠንካራና ተለዋዋጭ የሕዝብና የግል አጋርነት እንዲሁም በግሉ ዘርፍ ንቁ ተሳትፎ መሆኑን ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2019 የጀመረችውን የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀምሌ 2024 ወደ ላቀ ደረጃ በማሸጋገር የውጭ ምንዛሪ ተመን በገበያ እንዲወሰን ማድረጓን አስታውሰዋል። ከዚህም በተጨማሪ ዘመናዊ የገንዘብ ፖሊሲና ጠንካራ የታክስ አስተዳደር ስርዓት መዘርጋቱን ጠቅሰው፣ የመንግስት የልማት ድርጅቶች ሪፎርም ተደርገው ቁልፍ የኢኮኖሚ ዘርፎች ለግሉ ዘርፍ ክፍት ሆነዋል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም ከጥቂት ዓመታት በፊት ለውጭ አልሚዎች ትልቅ ፈተና የነበረው የውጭ ምንዛሪ አቅርቦት ችግር በሪፎርሙ አማካኝነት ሊፈታ መቻሉንም አረጋግጠዋል፡፡ ይህ ማክሮ-ኢኮኖሚያዊ ሪፎርም በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጨባጭና ገንቢ ውጤቶችን ማስመዝገቡንም አብራርተዋል፡፡ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚው ሪፎርም የሀገር ውስጥ ገቢ በ61 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን ጠቅሰዋል፡፡ ወደ ውጭ የሚላከው የምርት መጠን በ119 በመቶ እድገት ማስመዝገቡንም ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከ120 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ያላት፣ በአፍሪካ ትልቁ ገበያና እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ባለቤት መሆኗን ያነሱት ሚኒስትሩ፤ የውጭ ባለሀብቶች በተለያዩ ዘርፎች ላይ እንዲሰማሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ግብርና የሀገሪቱን ጥቅል ሀገራዊ ምርት (GDP) 40 በመቶ የሚሸፍን፣ 80 በመቶ የሚሆነውን የውጭ ምንዛሪ ገቢ የሚያስገኝና 75 በመቶ የሥራ ዕድል የፈጠረ የኢኮኖሚው ምሰሶ ነው ብለዋል፡፡ የውጭ ባለሀብቶች በዘመናዊ ግብርና፣በግብርና ምርቶች ማቀነባበርና እሴት መጨመር ላይ በስፋት በመሰማራት ውጤታማ መሆን እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡ ሀገሪቱ የአምራች ኢንዱስትሪውን ምርታማነት ለማሳደግ፣ ለተኪ ምርቶች ትኩረት ለመስጠትና ከዓለም አቀፍ የእሴት ሰንሰለት ጋር ለመቀላቀል ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ “የኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ በስፋት እየተተገበረ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡ ወርቅን ጨምሮ ሌሎች ወሳኝና ስትራቴጂካዊ ማዕድናት መገኛ በሆነችው ኢትዮጵያ ውስጥ በዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ የሪፎርም ተግባራት በርካታ የውጭ ኢንቨስተሮችን እየሳቡ እንደሚገኙም ጠቁመዋል፡፡ የኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት ሁኔታ ከበፊቱ ሙሉ በሙሉ መቀየሩን ጠቁመው፤ የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን በማስፋፋትና ተቋማትን በማጠናከር እጅግ ምቹ የኢንቨስትመንት ከባቢ መፈጠሩን ገልጸዋል። የሪፎርም አጀንዳው ዋነኛ ትኩረት ተቋማትን ማጠናከር እንደሆነና ይህም የዓለም የንግድ ድርጅት አባልነትን ጨምሮ ከዓለም አቀፍ ደረጃዎች ጋር የተጣጣመና የኢንቨስተሮችን መብትና ፍላጎት ማዕከል ያደረገ መሆኑን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የግሉን ኢንቨስትመንት እንደ ረጅም ጊዜ የልማት አጋር እንደምትመለከት የገለጹት ሚኒስትሩ፤ የእንግሊዝ ባለሀብቶችና የንግዱ ማህበረሰብ በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች እንዲሰማሩ በሯ ክፍት መሆኑን በማረጋገጥ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
ኢትዮጵያ ታከናውናለች፡ በግብርናው ዘርፍ የተመዘገቡ ሁለንተናዊ ስኬቶችና መዋቅራዊ ሽግግሮች
Jun 25, 2026 216
በለውጡ ዓመታት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት በሆነው በግብርናው ዘርፍ ላይ የተከናወኑት ሁለንተናዊ የፖሊሲ ማሻሻያዎች በዘርፉ ተጨባጭ የሆነ መዋቅራዊ ሽግግር እንዲመዘገብ አድርጓል። መንግሥት ለዘርፉ የሰጠው ልዩ ትኩረትና የተቀረጹ ስትራቴጂካዊ ስልቶች፣ ግብርናውን በአንድ ወጥ ሰብል (Monoculture) እና በዝናብ ላይ ብቻ ከተመሰረተ አካሄድ በማውጣት፣ ወደ ተደራጀ፣ ምርታማና የብዝሃ-ሕይወት አቅምን ወደሚያሳድግ ዘመናዊ የኢኮኖሚ ምሰሶነት ቀይረውታል። ይህ ስኬት ጥቂት ዘርፎች ላይ ብቻ ሳይሆን በሰብል ልማት፣ በእንስሳት ሀብት፣ በሆርቲካልቸር፣ በደንና ተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ፣ በሜካናይዜሽን እንዲሁም በገበያና አግሮ-ኢንዱስትሪ ትስስር ዙሪያ ሰፊ ውጤቶችን አምጥቷል። በሰብል ልማት ረገድ የተመዘገበው ታሪካዊ ስኬት በበጋ መስኖ ስንዴ አብዮት የሚገለጽ ሲሆን፣ ዝናብን ብቻ የመጠበቅን ልማድ በመስበርና ሰፊ የመስኖ መሠረተ-ልማትን በመጠቀም ኢትይጵያ ለአገር ውስጥ ፍጆታ የምታደርገውን የከፍተኛ ስንዴ ግዢ በማስቀረት ራሷን ችላለች። ከዚህም ባለፈ፣ የተረፈውን ምርት ወደ ውጭ ሀገራት መላክ የተጀመረበት አዲስ ታሪካዊ ምዕራፍ የተፈጠረ ሲሆን፣ ከስንዴ በተጨማሪም እንደ አኩሪ አተር፣ ሰሊጥ ያሉ የቅባትና ጥራጥሬ እህሎች ምርታማነት በክላስተር አሰራር በማደጉ ለአገር ውስጥ የምግብ ዘይት ፋብሪካዎች አስተማማኝ የጥሬ እቃ ግብአት ዋስትና ፈጥሯል። በእንስሳት ሀብት ልማት በኩል የተጀመረው የሌማት ትሩፋት ብሔራዊ ኢኒሼቲቭ በአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ኑሮ ላይ ለውጥ ያመጣ ሌላኛው የስኬት ማሳያ ነው። በአፍሪካ ቀዳሚ የሆነውን የእንስሳት ሀብት ወደ ተጨባጭ ጥቅም ለመቀየር በተደረገው ጥረት የተሻለ ዝርያ ያላቸው የውጭና የሀገር ውስጥ ድቅል የወተት ላሞች ስርጭት በመጨመሩ፣ የዘመናዊ መኖ አቅርቦት በመሻሻሉ፣ እንዲሁም በከተማ ግብርና ጭምር በተስፋፋው የዶሮና የንብ እርባታ የወተት፣ የሥጋ፣ የእንቁላልና የንፁህ ማር ምርት በከፍተኛ ሁኔታ አድጓል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በታላላቅ ግድቦችና በሰው ሰራሽ ኩሬዎች ላይ እየተከናወነ ያለው የአሳ ሀብት ልማት ሥራ የሕዝቡን የሥነ-ምግብ (Nutritional) እና የፕሮቲን ፍላጎት ለማሟላት ትልቅ አቅም እየሆነ ይገኛል። የሆርቲካልቸር (የአትክልትና ፍራፍሬ) እና የኢኮኖሚ ሰብሎች ልማትም የሀገሪቱን የኤክስፖርት አድማስ ያሰፋ ሌላኛው ስኬታማ ዘርፍ ነው። የተሻሻሉ የአቮካዶ (Hass Avocado) እና የሙዝ ዝርያዎች በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በስፋት በመልማታቸው፣ ምርቶቹ በቀጥታ ወደ አውሮፓና መካከለኛው ምስራቅ ገበያ መላክ የጀመሩ ሲሆን፣ የሀገሪቱ ቀዳሚ የውጭ ምንዛሬ አስገኝ የሆነው ቡናም የአመራረት ዘዴው በመሻሻሉና በቀጥታ ለአምራቹ በሚከፈልበት የገበያ ትስስር (Vertical Integration) ምክንያት በየዓመቱ ከፍተኛ የምርትና የገቢ ሪከርድ እያስመዘገበ ይገኛል። የግብርናው ዘላቂነትና ምርታማነት የተረጋገጠው ደግሞ ቴክኖሎጂንና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃን በአግባቡ ማቀናጀት በመቻሉ ነው። መንግሥት ለትራክተሮች፣ ኮምባይነሮች እና የውሃ ፓምፖች ያደረገው የቀረጥ ነፃ መብት ተለምዷዊውን የእርሻ ስራ ወደ መካከለኛና ከፍተኛ ሜካናይዜሽን አሰራር የቀየረው ሲሆን፣ በቴክኖሎጂው ዘርፍ ድሮኖች (Drones) ለፀረ-ተባይ ርጭትና ለምርት ክትትል ጭምር ጥቅም ላይ መዋል ጀምረዋል። ይህ የቴክኖሎጂ ዕድገት በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከተከናወነው የተፈጥሮ ሀብትና የአፈር ጥበቃ ሥራ ጋር በመቀናጀቱ፣ የከርሰ ምድር ውሃ እንዲያገግም፣ የአፈር መሸርሸር እንዲቀንስና ለመስኖ ግብርና ምቹ ሁኔታ እንዲፈጠር አድርጓል። የተመዘገቡት ስኬቶች በሙሉ ዘላቂ የገበያ ዋስትና እንዲኖራቸው ለማድረግ የምርት ብክነትን ከሚቀንሱና እሴት ከሚጨምሩ የተቀናጁ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ጋር ሰፊ የገበያ ትስስር ተፈጥሯል። አርሶ አደሩ የሚያመርታቸው የሰብልና የእንስሳት ምርቶች በቀጥታ በሀገር ውስጥ ወደተገነቡት የምግብና መጠጥ ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎች እንዲገቡ መደረጉ፣ ለአርሶ አደሩ አስተማማኝ ገበያ ከመፍጠሩም በላይ ሀገሪቱ ከግብርና ምርት ጥሬ ዕቃ ላኪነት ወደ እሴት የተጨመረበት (Value-added) ምርት ላኪነት እንድትሸጋገር ትልቅ መዋቅራዊ መሠረት ጥሏል። በአጠቃላይ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የኢትዮጵያ ግብርና ሁሉንም ክፍሎች ያካተተ ሁለንተናዊ የብዝሃ-ዘርፍ ዕድገት በማስመዝገብ ላይ ይገኛል። ይህም የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተከናወነ ላለው ስራ ምቹ መደላድልን ፈጥሯል።
በክልሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ድጋፍ ሊጠናከር ይገባል 
Jun 25, 2026 210
ጋምቤላ፤ ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለተያዘው ግብ መሳካት፣ የባለድርሻ አካላት ድጋፍና ትብብር ሊጠናከር እንደሚገባ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሯን ጨምሮ የክልልና የፌደራል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ በአቦቦ ወረዳ በሩዝ ሰብል ላይ እየተካሄደ ያለውን የምርምር ሥራ ዛሬ ጎብኝተዋል።   ርዕሰ መስተዳድሯ በወቅቱ እንዳሉት፤ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚቻለው የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ማስፋፋትና ተደራሽ ማድረግ ሲቻል ነው። ክልሉ ያለውን ሰፊ የመሬትና የውኃ ሀብት በምርምር መደገፍ ከተቻለ፣ ለአካባቢው ብቻ ሳይሆን ለሀገር የሚተርፍ የሰብል ምርት ማግኘት እንደሚቻልም ተናግረዋል። ጋምቤላ ለሁሉም የግብርና ልማት ዓይነቶች ምቹ ሥነ-ምህዳር ያላት መሆኑን የጠቀሱት ወይዘሮ ዓለሚቱ፤ በተለይም የሩዝ ሰብል አዋጭ ተብለው ከተለዩት የሰብል ዓይነቶች በቀዳሚነት የሚጠቀስ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የሩዝ ልማትን ማዘመንና ማስፋፋት ከተቻለ ለአገር ውስጥ ፍጆታ አልፎ ለውጭ ገበያ የሚተርፍ ምርት ማግኘት እንደሚቻልም አክለዋል።   ልማቱን ለመደገፍ በባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት፣ በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲና በቻይናው ዩናን ዩኒቨርሲቲ ቅንጅት እየተካሄደ ያለው የምርምር ሥራ የሚበረታታ መሆኑን በመግለጽ፣ ለሥራው ስኬታማነት የክልሉ መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍና ትብብር እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሀብት ልማት፣ የሥራ ስምሪትና የቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ እንደ ሀገር የታለመውን የግብርና ልማት ስኬታማ ማድረግ የሚቻለው አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ ለአርሶ አደሩና ለባለሀብቱ ተደራሽ ማድረግ ሲቻል መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም በተለያዩ ተቋማት ትብብር በሩዝ ሰብል ላይ የተጀመረው የምርምር ሥራ ተስፋ ሰጪና ዘርፉን የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል።   የባዮና ኢመርጂንግ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ካሳሁን ተስፋዬ በበኩላቸው፤ የምርምር ሥራው እየተካሄደ ያለው ከቻይናው ዩናን ዩኒቨርሲቲ ጋር መሆኑን አስረድተዋል። የአዲሱ የሩዝ ዝርያ ልዩ ባህሪያት መካከል በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚደርስ መሆኑ እንዲሁም በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ መመረቱ እንደሆነ ገልጸዋል። በሩዝ ዝርያዎቹ ላይ እየተካሄደ ያለው የማላመድ የምርምር ሥራ በሚቀጥለው ዓመት ተጠናቆ ለተጠቃሚዎች ተደራሽ እንደሚሆንም ዋና ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን ከ117 ሺህ በላይ ወጣቶችን የስራ እድል ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል- መምሪያው
Jun 25, 2026 145
ደብረ ማርቆስ ፤ሰኔ 18/2018(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን ባለፉት 11 ወራት ከ117 ሺህ በላይ ወጣቶች የስራ እድል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የዞኑ ስራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ፀሐይ ቦጋለ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ለበርካታ ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር የተቻለው የአካባቢውን ጸጋ በጥናት በመለየትና አልምቶ ለመጠቀም በተደረገ ጥረት ነው። በአጠቃላይ በበጀት ዓመቱ ከ 131 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር የታቀደ ሲሆን ባለፉት 11 ወራት 117 ሺህ 427 የሚሆኑ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። የተፈጠረው የስራ እድል በማዕድን ልማት ፣ በኮንስትራክሽን ፣ በግብርና ፣ በአምራች ኢንዱስትሪዎችና ሌሎች መስኮች መሆኑን ነው የጠቆሙት ። በዚሁ ወቅት የስራ እድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ከ30 በመቶ በላይ የሚሆኑት በተለያዩ መስኮች ትምህርታቸውን ተከታትለው የተመረቁ መሆናቸውንም አንስተዋል። የስራ እድል ለተፈጠረላቸው ዜጎች 491 ሚሊየን ብር በላይ ብድር፣ ከ270 በላይ የመስሪያ ሼድና ኮንቴነሮች ድጋፍ መደረጉን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም በገጠርና በከተማ በግብርና ዘርፎች ስራ ለተፈጠረላቸው ዜጎች ከ15 ሺህ ሄክታር በላይ የእርሻ መሬት በመስጠት ወደ ስራ ማስገባት መቻሉን አብራርተዋል። በዞኑ የባሶሊበን ወረዳ የጁቤ ከተማ ነዋሪ ወጣት ቀለምወርቅ ገነት ፤ ከሶስት ጓደኞቹ በመደራጀት ወደ ግብርና ስራ ገብቶ ተጠቃሚ መሆን መጀመሩን ነው የሚናገረው ። የተፈጠረለት የስራ እድል ከቤተሰብ ጥገኝነት በማውጣት ገቢ ለማግኝት ከማስቻሉ ባሻገር ሀብት ለማፍራት እንዳስቻለው ነው ያመለከተው። የአዋበል ወረዳ የሉማሜ ከተማ ነዋሪ ወጣት ጌትነት ይመር በበኩሉ፤በዘንድሮው ዓመት ከአምስት ጓደኞቹ ጋር በመደራጀት በኮንስትራክሽን ዘርፍ የብሉኬት ምርት ላይ መሰማራቱን ነው የሚናገረው። በመንግስት በተመቻቸላቸው የመስሪያ ቦታን ጨምሮ የ500 ሺህ ብር ብድርና ሌሎች ድጋፎች በመነሳት ወደ ስራ ተሰማርተው ገቢ ማግኝት መጀመራቸውን ነው የሚናገረው።  
የጉባ ብስራቶች -የኢትዮጵያ የማከናወን ጉዞ ቀጣይነት ማሳያዎች
Jun 25, 2026 256
ኢትዮጵያ እየተገበረች ያለው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ (Homegrown Economic Reform) መዋቅራዊ ማነቆዎችን በመስበር ረገድ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ከፍቷል። ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሙሉ ለሙሉ መጠናቀቁ በተበሰረበት ታሪካዊ ወቅት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ይፋ ያደረጓቸው "የጉባ ብስራቶች" ሀገሪቱ በኃይል፣ በኢንዱስትሪ፣ በአቪዬሽን፣ በማዕድንና በከተማ ልማት ዘርፍ የደረሰችበትን ከፍተኛ የማስፈጸም አቅም ያሳዩ ሲሆን፣ እነዚህ ግዙፍ ፕሮጀክቶች "ኢትዮጵያ ታከናውናለች" የሚለውን አገራዊ መርህ በተግባር የሚያረጋግጡ ናቸው። ለጉባ ብስራቶች ዋነኛ ምሰሶ የነበረውና ለመላው አፍሪካ ኩራት የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴው ግድብ ግንባታ ሙሉ በሙሉ ፍጻሜ ማግኘቱ የሪፎርሙ ውጤታማነት ትልቁ ማሳያ ነው። የለውጡ መንግስት የፋይናንስ ማነቆዎችን በቁርጠኝነት በመፍታት እንዲሁም ዲፕሎማሲያዊ ጫናዎችን በመቋቋም ግድቡን አጠናቅቆ ሌላ ሜጋ ፕሮጀክቶችን ጀምሯል። ይህም በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ውስጥ አንዱ የታሪክ እጥፋት ነው። ኢትዮጵያ የወደፊት የኃይልና የቴክኖሎጂ ፍላጎቷን በዘላቂነት ለማረጋገጥ የኒውክሌር ኃይልን ለሰላማዊ አገልግሎት ለማዋል የጀመረችው ታሪካዊ ጉዞ ሌላኛው ደማቅ ብስራት ነው። በሪፎርሙ ወቅት ከዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር የተደረጉት ስምምነቶችና የተጀመሩት የዝግጅት ስራዎች፣ ሀገሪቱ በሕክምና፣ በግብርና እና በኃይል አማራጮች ላይ ያላትን የረጅም ጊዜ አርቆ አሳቢነትና የከፍተኛ ቴክኖሎጂ ሽግግር ቁርጠኝነት ያሳያሉ። በሌላ በኩል የኢትዮጵያን የአቪዬሽን መሪነትና የኮሜርስ የበላይነት በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማስቀጠል የታለመው የአዲሱ የቢሾፍቱ ሜጋ አየር ማረፊያ (Bishoftu International Airport) በፍጥነት እየተከናወነ ይገኛል። ሙሉ ለሙሉ ሲጠናቀቅ በዓመት ከ110 ሚሊየን በላይ መንገደኞችን ግዙፍ የጭነት አውሮፕላኖችን ለማስተናገድ የተነደፈው ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት፣ ሀገሪቱን የአፍሪካ ዋና የትራንስፖርትና የሎጂስቲክስ መገናኛ ኮሪደር የማድረግ ስትራቴጂ አካል ነው። ከዚህ በተጨማሪ በማዕድን ዘርፍ ለዘመናት ሲጠበቅ የነበረውን አገራዊ እምቅ አቅም ወደ ጥቅም ለመቀየር በኦጋዴን ተፋሰስ የተገነባው የተፈጥሮ ጋዝ ፋብሪካ ተጠናቆ በስኬት ተመርቋል። ይህ ሜጋ ፕሮጀክት ሀገሪቱ የራሷን የሃይልና የኢንዱስትሪ ግብዓት እንድታመርት አቅም የፈጠረ ሲሆን፣ ለሀገር ውስጥ የኬሚካል ኢንዱስትሪዎች ትልቅ መነቃቃትን የፈጠረ የሪፎርሙ ታላቅ ስኬት ነው። የግብርናውን ዘርፍ ምርታማነት በዘላቂነት ለማረጋገጥና በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የሚገባውን ግብዓት በሀገር ውስጥ ለመተካት የግዙፍ ማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ በይፋ ተጀምሯል። ይህ ፕሮጀክት አርሶ አደሩን ከውጭ አቅራቢዎች ጥገኝነትና ከተደጋጋሚ የእጥረት አደጋዎች የሚታደግ ከመሆኑም በላይ፣ የሀገሪቱን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የተነደፈ ስልታዊ የሪፎርሙ አካል ነው። ኢትዮጵያ በነዳጅ አቅርቦት ላይ ያላትን የውጭ ምንዛሬ ጫና ለማቃለልና የኢነርጂ ዋስትናዋን ለማጠናከር የጀመረችው የነዳጅ ማጣሪያ ግንባታ ሌላኛው ስትራቴጂካዊ የጉባ ብስራት ነው። በከተማ ልማትና በዜጎች የኑሮ ደረጃ መሻሻል ረገድ ትልቁ አገራዊ ንቅናቄ የሆነው የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት በከፍተኛ ፍጥነት በቴክኖሎጂ በመታገዝ ጭምር እየተተገበረ ይገኛል። ይህ ፕሮጀክት የቤት ተደራሽነትን ከማሻሻሉም በላይ ለበርካታ ወጣቶች የስራ እድልና የእውቅት ሽግግር ለመፍጠር ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው። በአጠቃላይ የጉባ ብስራቶች ኢትዮጵያ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ጉዞ ውጤታማነትን የሚያመላክቱና ኢትዮጵያ ለቀጣዩ ትውልድ ዘላቂ ብልጽግናንና የኢኮኖሚ ነፃነትን የሚያረጋግጥ ታሪካዊ መሰረት እየጣለች ለመሆኑ ህያው ምስክሮች ናቸው።
በበጀት ዓመቱ 11 ወራት ለውጭ ገበያ ከቀረቡ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች 117 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ተገኝቷል
Jun 25, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ):- በበጀት ዓመቱ 11 ወራት ለውጭ ገበያ ከቀረቡ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች 117 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን የኢትዮጵያ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አስራት ጤራ (ዶ/ር) አስታወቁ፡፡ ኢትዮጵያ የተለያዩ የእንስሳት ምርትና ተዋጽኦን በማቀነባበር ለውጭ ገበያ በማቅረብ የውጭ ምንዛሪ ገቢ ታገኛለች፡፡ የኢትዮጵያ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አስራት ጤራ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ካላት እምቅ የእንስሳት ሀብት ተገቢውን የውጭ ምንዛሪ ገቢ እንድታገኝ የእንስሳትን ምርታማነት የሚያሳድጉ አሰራሮች ተጠናክረው ይቀጥላሉ፡፡ ኢንስቲትዩቱ የእንስሳት ዝርያዎችን ለማሻሻል አዳዲስ የፈሳሽ ናይትሮጅን ማምረቻ ማዕከላትን እያሰፋና ነባሮችን እያዘመነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም በበጀት ዓመቱ 11 ወራት ለውጭ ገበያ ካቀረባቸው የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች 117 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ተገኝቷል፤ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የስድስት ሚሊዮን ዶላር ብልጫ አለው ብለዋል፡፡ ለውጭ ገበያ ከቀረቡ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች መካከል የበግና ፍየል ስጋ እንዲሁም የእርድ ተረፈ ምርቶች ቀዳሚዎች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የሥጋ ምርቶቹ በብዛት ወደ ውጭ ከተላኩባቸው ሀገራት መካከል የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ ሳውዲ አረቢያ፣ ኳታር መሆናቸውን ገልጸው፤ ወደ አፍሪካ ሀገራትም ይቀርባሉ ብለዋል፡፡ በአማራ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የደብረ ብርሃን ግብርና ምርምር ማዕከል የእንስሳት ጤና እና ሥነ ተዋልዶ ተመራማሪ ዶክተር ቸኮል ደምስ፤ የእንስሳት ምርታማነትን ለማሳደግ በዘርፉ ለተሰማሩ ዜጎች የእንስሳት እርባታ ሳይንስ ላይ በቂ ግንዛቤ እንደሚሰጡ ገልጸዋል፡፡ ማዕከሉ የተሻሻሉ የበግና የዳልጋ ከብት ኮርማዎች ተገቢውን እንክብካቤ አግኝተው እንዲያድጉ ለማድረግ በምርምር የተደገፈ እገዛ ያደርጋል ብለዋል፡፡ በአርባ ምንጭ ግብርና ምርምር ማዕከል የእንስሳት ጤና ማሻሻያ ተመራማሪ ዶክተር ናሆም በላይ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የእንስሳት ሀብት ልማትን የሚያሳድግ ፍሬያማ ውጤት መገኘቱን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም በዘርፉ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የዘርፉ ባለሙያዎች ልምዳቸውን ለእንስሳት ሀብት ልማት ማዋል እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡    
በኦሮሚያ ክልል የተከናወኑ የመስኖ ልማት ሥራዎች ዜጎችን ከተረጂነት አውጥተዋል
Jun 25, 2026 241
ሮቤ፣ሰኔ 18/2018(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል የአርሶና አርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ የተከናወኑ የመስኖ ልማት ሥራዎች ዜጎችን ከተረጂነት በማውጣት ራሳቸውን እንዲችሉ ዕድል መፍጠሩን የክልሉ የመስኖ ልማትና አርብቶ አደር ቢሮ ገለጸ። የቢሮው ምክትል ኃላፊና የአርብቶ አደር ልማት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ሮባ ቱርቼ በተለይ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአርሶና አርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስና የኑሮ ሁኔታወን ለማሻሻል በርካታ ሥራዎች ተከናውነዋል። በክልሉ በለውጡ ዓመታት የሕዝቡን የድርቅ ተጋላጭነት የመቋቋም አቅም ለማሳደግ ከተሰሩት ሥራዎች መካከል የመስኖ ልማት ማስፋፊያ ፕሮጀክቶች ግንባታ ሥራዎች አንዱ ነው ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እና አርሶና አርብቶ አደሩ በዝናብ ላይ ብቻ ጥገኛ እንዳይሆን ለማድረግ ለመስኖ ማስፋፊያ ፕሮጀክቶች ትኩረት ተሰጥቶ ሲሠራ መቆየቱንም አስታውሰዋል። በ2018 የበጀት ዓመት ብቻ የአርብቶ አደሩንና የከፊል አርብቶ አደሩን የድርቅና አደጋ መቋቋም አቅም የሚያሳድጉ 256 የሚሆኑ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመው ከተገነቡት የመስኖ ፕሮጀክቶች መካከል 56 በመቶው የሚገኙት በአርብቶ አደር አካባቢዎች ነው ብለዋል። በተለይም 'ፊና' በተሰኘ ፕሮግራም አማካኝነት ወደ ግንባታ ከገቡ 73 የመስኖ ግድቦች መካከል 38ቱ ተጠናቀው በአሁኑ ወቅት 78 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ለሰውና ለእንስሳት መጠጥ የሚውል ውኃ የመያዝ አቅም መፍጠራቸውን ገልጸዋል። አቶ ሮባ እንዳሉት፣ የክልሉ መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት ባለፉት አምስት ዓመታት አንድ ሺህ የሚሆኑ ትላልቅ፣ መካከለኛና አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን ተናግረዋል። በዚህም በክልሉ ቀደም ሲል ከ70 ሺህ ሄክታር የማይበልጠው በመስኖ የሚለማው መሬት በአሁኑ ወቅት ወደ 3 ነጥብ 8 ሚሊዮን ሄክታር ማሳደግ ተችሏል። የልማት ፕሮጀክቶቹ በተለይ በቆላማ የክልሉ አካባቢዎች እውን መሆን ቀደም ሲል በሴፍቲኔት ዕርዳታ ይተዳደሩ የነበሩ ዜጎችን በመስኖ አማራጭ በመሳተፍ ራሳቸውን እንዲችሉ ዕድል መፍጠሩን የባሌና ምስራቅ ባሌ ዞን አርብቶ አደሮችን በማሳያነት አንስተዋል። በተጨማሪም በእነዚህ አካባቢዎች በተሰሩ ግድቦች የተከማቸ ውሃ ለሰውና ለእንስሳት መጠጥ ከማገልገሉ ባለፈ፣ አርብቶ አደሩ በአሳ እርባታ ስራ ተሰማርቶ አዲስና አማራጭ የገቢ ማግኘት መጀመሩንም ገልጸዋል።   የባሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሀኪም አልይ በበኩላቸው እንዳሉት ፤ በዞኑ የአርሶና አርብቶ አደሩ የምግብ ዋስትና እንዲረጋገጥ የዝናብና ሌሎች የውኃ አማራጮች በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውሉ በትኩረት እየተሠራ ነው። በዞኑ የተለያዩ አማራጮችን በመጠቀም ከ500 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት በመኽር እርሻ ብቻ በዝናብ እንደሚለማ ጠቁመዋል። እንዲሁም የተለያዩ የመስኖ አማራጮችን በመጠቀም ከ170 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት ሁለት ጊዜና ከዚያ በላይ እየለማ እንደሚገኝ ተናግረዋል። አርብቶ አደሩን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ ትኩረት አግኝተው ሲሠራባቸው መቆየታቸውን አስታውሰዋል። በዞኑ የደሎ መና ወረዳ ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁት የዌልመልና ያዶት የመስኖ ፕሮጀክቶች የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት በመቀነስ ሕይወቱ እንዲሻሻል እያገዙ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይ የፕሮጀክቶቹ ወደ ሥራ መግባት ከዚህ በፊት በሴፍቲኔት ጠባቂነት የሚታወቁ የአካባቢው አርብቶ አደሮች ከመስኖ እርሻ ጋር በመተዋወቅ የምግብ ዋስትናቸውን እንዲያረጋግጡ እያገዘ መምጣቱንም አክለዋል።  
በኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት ድርድር ማዕቀፍ ኢትዮጵያ እና ኒውዚላንድ የሁለትዮሽ የገበያ ዕድል ስምምነት ተፈራረሙ
Jun 25, 2026 289
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 18/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅት (WTO) አባል ለመሆን የምታደርገው የድርድር ሒደት አካል የሆነውን የሁለትዮሽ የገበያ ዕድል ፕሮቶኮል ከኒውዚላንድ ጋር ተፈራርማለች። ስምምነቱ ኢትዮጵያ ወደ ዓለም አቀፉ የባለብዙ ወገን የንግድ ሥርዓት ለመቀላቀል ለምታደርገው ጉዞ ትልቅ ታሪካዊ ምዕራፍ መሆኑ ተገልጿል። በሁለቱ ሀገራት መካከል ለረጅም ጊዜ ሲካሔድ የነበረውን የሁለትዮሽ ድርድር ያጠናቀቀው ይህ ስምምነት፣ በሸቀጦችና በአገልግሎት ዘርፎች ላይ በጋራ የተደረሱ የገበያ ተደራሽነት ግዴታዎችንና ጥቅሞችን ያካተተ ነው። ፕሮቶኮሉን በጄኔቫ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እና ሌሎች ዓለም አቀፍ ድርጅቶች የኢትዮጵያ ቋሚ መልዕክተኛ እና አምባሳደር ፀጋአብ ከበበው እና በዓለም ንግድ ድርጅት የኒውዚላንድ ቋሚ መልዕክተኛ አምባሳደር ክሌር ኬሊ ፈርመውታል።   ይህ ስምምነት ሁለቱ አገራት ግልጽነት የሰፈነበት፣ በሕግ የሚመራ እና ልማትን ማዕከል ያደረገ የባለብዙ ወገን የንግድ ሥርዓት ለመገንባት ያላቸውን የጋራ ቁርጠኝነት የሚያንጸባርቅ መሆኑ በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ተመላክቷል። የኒውዚላንድ ቋሚ መልዕክተኛ አምባሳደር ክሌር ኬሊ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በአፍሪካ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት በማስመዝገብ ላይ የምትገኝ አገር መሆኗን በማንሳት የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ስትሆን ከሌላው ዓለም ጋር የሚኖራትን የኢኮኖሚ ትስስር ለማጠናከር ዕድል እንደሚሰጣት ገልጸዋል። አያይዘውም አገራቸው የኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት ሒደት በመደገፍ ረገድ የምታደርገውን አስተዋጽኦ አጠናክራ ለመቀጠል ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል። በተጨማሪም ስምምነቱ በሁለቱ አገሮች መካከል ያለውን የንግድ እና ኢንቨስትመንት ግንኙነት ለማጠናከር የተሻለ ዕድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል። አምባሳደር ፀጋአብ ከበበው በበኩላቸው በድርድሩ ሂደት ኒውዚላንድ ላሳየችው ገንቢ ተሳትፎ እና ቀጣይነት ላለው ድጋፍ ምስጋና ማቅባቸውን ኢዜአ ከስፍራው ያገኘው መረጃ ያመለክታል። ከሁለትዮሽ የንግድ ግንኙነቱ ባለፈ፣ ኢትዮጵያ እና ኒውዚላንድ በተለያዩ ዓለም አቀፍና ባለብዙ ወገን መድረኮች ላይ ያላቸውን የቅርብ ትብብር አጠናክረው ቀጥለዋል። በኒውዚላንድ እና በኢትዮጵያ መካከል ያለው የሁለትዮሽ ግንኙነት እያደገ የመጣ ሲሆን፣ ግንኙነቱ በዋናነት በግብርና ትብብር፣ በጂኦተርማል (የእንፋሎት) ኃይል ድጋፍና በቴክኒክ አገልግሎቶች ላይ ያተኮረ ነው።
ረቂቅ አዋጁ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት የምታደርገውን ጥረት የሚደግፍ ነው
Jun 24, 2026 1200
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት የምታደርገውን ጥረት የሚደግፍ መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ፡፡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የኢትዮጵያ የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅ ላይ ይፋዊ የሕዝብ መድረክ አካሂዷል፡፡ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት፤ በሕዝብ መድረኩ ለተሳተፉ አካላት ስለ ብሔራዊ የካርበን ግብይት ረቂቅ አዋጁ ይዘትና አስፈላጊነት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡   በማብራሪያቸው፤ የካርበን ግብይት የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የተዘረጋ ዓለም አቀፍ የንግድ ሥርዓት መሆኑን ጠቅሰው ዓላማውም ወደ ከባቢ አየር የሚለቀቀውን በካይ ጋዝ መጠን ማስወገድ፣ መቀነስ እና መከላከል ነው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ይህንን ለመተግበር በፖሊሲ የተደገፈ ተግባር እያከናወነች እንደምትገኝም ጠቁመው ይህም በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ማስገኘት መቻሉን ጠቁመዋል፡፡ በዛሬው ዕለት ለሕዝብ ውይይት ይፋ የተደረገው ረቂቅ አዋጅ በሀገራችን የካርበን ገበያ ልማት ላይ ወሳኝ ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑን ጠቅሰው የካርቦን ግብይት ኢትዮጵያ ከዘርፉ ተጨማሪ የፋይናንስ ምንጭ የምታገኝበት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የበካይ ጋዝ የልቀት መጠን እንዲቀንስ በማድረግ የአረንጓዴ እና የዘላቂ ልማት ግቦች እንዲሳኩ እንደሚያደርግም እንዲሁ፡፡ በሕዝብ መድረኩ የተሳተፉት የአረንጓዴ ዐሻራ ቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) በሰጡት አስተያየት፤ ረቂቅ አዋጁ ኢትዮጵያ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ የሰጠችውን ትኩረት በግልጽ የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅ የካርበን ግብይት ለሀገራችን እንደ አንድ ተጨማሪ የኢንቨስትመንት አማራጭ ሆኖ ስለሚያገለግል ሂደቱ በተፋጠነ መልኩ ወደ ተግባር መግባት እንዳለበት አመላክተዋል፡፡   በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጀ፤ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነቶችን ከፈረሙ ሀገራት አንዷ መሆኗን ገልጸዋል። ይህ የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅ የተበታተኑ አሠራሮችን ወደ አንድ በማምጣት፣ የካርበን ግብይትን በተሟላ እና ግልጽ በሆነ የሕግ ማዕቀፍ ለመምራት ያስችላል ብለዋል። ረቂቅ አዋጁ ሀገሪቱ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት የምታደርገውን ጥረት የሚደግፍና ለተግባራዊነቱ ትልቅ መሠረት የሚጥል መሆኑንም ጠቁመዋል። በተጨማሪም አረንጓዴ ልማትን እና የታዳሽ ኃይል አጠቃቀምን የሚያበረታታ በመሆኑ፣ ሀገራችን ከምታመነጨው የካርቦን ልቀት ገቢ እንድታገኝ ያደርጋታል ብለዋል። ይህ ወሳኝ ሰነድ ጸድቆ ወደ ተግባር ሲገባ የኢትዮጵያ የካርበን ግብይት ግልጽ መመሪያና ሥርዓት እንዲኖረው ለማድረግ ከፍተኛ እገዛ ይኖረዋል ብለዋል። በመሆኑም አዋጁ አስፈላጊዎቹን የዝግጅት ሒደቶች በሙሉ አልፎ ለትግበራ እንዲበቃ ቋሚ ኮሚቴው የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት አረጋግጠዋል።
በዞኑ የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች በስፋት እየተከናወኑ ነው
Jun 24, 2026 444
ጊምቢ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ወለጋ ዞን የህዝቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆናቸውን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በምዕራብ ወለጋ ዞን ቆንዳላ ወረዳ ግንባታቸው የተጠናቀቁ የተለያዩ መሰረተ ልማት ግንባታዎች ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተመርቀው ለአገልግሎት በቅተዋል።   በወቅቱም የኦሮሚያ ክልል የመንገድ እና ሎጂስቲክስ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ታዬ ጉዲሳ በክልሉ ህዝቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እየተከናወኑ ናቸው። መሰረተ ልማቱም በአጭር እና በረጅም ጊዜ እቅድ የተገነቡ መሆኑንና በህዝቡና በአጋር አካላት ተሳትፎ መከናወናቸውን ጠቅሰው ተግባራቱም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።   የክልሉ መንግስት የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ባለው ቁርጠኝነት በርካታ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን ያነሱት ኃላፊው ዛሬ በዞኑ የተመረቁት ፕሮጀክቶችም የዚሁ ማሳያ መሆናቸውን ተናግረዋል።   የምዕራብ ወለጋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ተሊላ ተረፈ በበኩላቸው በዞኑ ለነዋሪዎች የመሰረተ ልማት ጥያቄ ምላሽ የሚሰጡ ግንባታዎች በጥራትና በተያዘላቸው ጊዜ ተገንብተው ለአገልግሎት እንዲበቁ እየተሰራ ነው ብለዋል።   የዚሁ አካል የሆኑትና በበጀት ዓመቱ ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ መሠረተ ልማቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም በዞኑ የህዝቡን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል።          
በተደመረ አቅም የግብርና ምርታማነትን በማስፋትና በማሳደግ ከተረጂነት የመውጣት ጥረት በልዩ ትኩረት እየተሰራበት ነው- ርእሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Jun 24, 2026 1090
ዱራሜ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፦ በተደመረ አቅም የግብርና ምርታማነትን በማስፋትና በማሳደግ ከተረጂነት የመውጣት ጥረት በልዩ ትኩረት እየተሰራበት መሆኑን የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። "የተቀናጀ የግብርና ትጋት ለላቀ ምርታማነት" በሚል መሪ ሀሳብ የመኸር ወቅት የተቀናጀ የግብርና ልማት ስራዎች የንቅናቄ መድረክ በዱራሜ ከተማ ተካሄዷል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በክልሉ ከተረጂነት ለመውጣት እየተደረገ ያለውን ጥረት የሚያግዙ የግብርናው ዘርፍ የልማት ስራዎች ይጠናከራሉ። በክልሉ በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ በሚገኙ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ጠቁመው፤ በዚህም የማህበረሰቡ ተጠቃሚነት እያደገ ስለመምጣቱም አስረድተዋል። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ትግበራም የኑሮ ውድነትን በማረጋጋት ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማበርከት ላይ ይገኛል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ ተግባሩን ማላቅ እንደሚገባም ጠቁመዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር በበኩላቸው በክልሉ በ2018/19 የመኸር ወቅት 800 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ ማሳ ይለማል ብለዋል።   በዚህም 70 ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ምርት ለማምረት ግብ ተቀምጦ ወደ ስራ መገባቱን ጠቁመዋል። ክልሉ የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ እያከናወናቸው በሚገኙ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በተለይም የአካባቢን ፀጋ ለይቶ በማልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የተጀመረው እሳቤ እውን በማድረግ የማህበረሰቡ ተጠቃሚነት እያደገ ስለመምጣቱም ጠቁመዋል። በዚህም አርሶ አደሩ ከቤት ፍጆታው አልፎ ለገበያና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ምርቶችን ማምረት ስለመጀመሩና ተግባሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል። የንቅናቄ መድረኩ በመኸር ወቅት የታቀደውን ግብ ለማሳካት የጋራ ተግባቦት ለመፍጠር እንደሚያግዝና አመራሩና የግብርና ባለሙያው ለእቅዱ መሳካት የበኩሉን አስተዋጽኦ ሊያበረክት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የከምባታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አረጋ እሸቱ በበኩላቸው በዞኑ የመኸር ወቅት የግብርና ልማት 47 ሺህ ሄክታር ማሳ ስንዴንና ገብስን ጨምሮ በሌሎች ዋና ዋና ሰብሎች ይለማል ብለዋል። በዞኑ የኩታ ገጠም እርሻ ትግበራ ለምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ጠቅሰው በመኸር ወቅት የግብርና ልማትም ስነ-ዘዴው በትኩረት ተግባራዊ እንደሚደረግም ገልጸዋል።
በክልሉ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን ተደራሽ የማድረግ ተግባር ይጠናከራል-ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)
Jun 24, 2026 360
ሚዛን አማን፣ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን ተደራሽ የማድረግ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በሚዛን አማን ከተማ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።   የሚዛን አማን መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የ5 ኪሎሜትር ኮሪደር ልማትና የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት መስጫ መናኸሪያ ዛሬ ተመርቀዋል ። ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት በክልሉ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ልማቶችን ማስፋፋትና ተደራሽ ማድረግ ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሠራ ነው።   በዚህ እንቅስቃሴ ውሰጥ የሕዝቡ ተሳትፎ እያደገ በመምጣቱ ትላልቅ መሠረተ ልማቶችን በመገንባት ለአገልግሎት ማዋል እየተቻለ መሆኑን ገልጸዋል። ዛሬ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው የሚዛን አማን መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት በቴክኖሎጂ ታግዞ ተቋማትን በማስተሳሰር ተገልጋዮችን ከብልሹ አሠራር የሚታደግ ነው ብለዋል። መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ጠቅሰው በሌሎች የክልሉ ከተሞችም ተደራሽ ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል።   በተመሳሳይ ዛሬ ወደ አገልግሎት የገባው የሚዛን አማን መናኸሪያ የትራንስፖርት አገልግሎትን የሚያሳልጥ መሆኑን ጠቁመዋል። የኮሪደር ልማት ስራም ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አስታውቀዋል።   የቤንች ሸኮ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን በዞኑ በመንግስትና በህዝብ ተሳትፎ የተከናወኑ የልማት ፕሮጀክቶች ፍትሀዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ መሆናቸውን ተናግረዋል።   ለዚህም ለምረቃ የበቃውን የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎትን ለአብነት ጠቅሰዋል ። የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር ሰለሞን ሌዊ በከተማው የተመረቁ ፕሮጀክቶች ለሕዝብ ጥያቄ ምላሽ የሰጡ መሆናቸውን ተናግረዋል ። የልማት ፕሮጀክቶቹ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው መሆኑን ገልጸዋል።   ህብረተሰቡን በማሳተፍ ከተማውን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ የማድረግ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል ። ከከተማው ነዋሪዎች መካከል አቶ ያሲን የካ እና ወይዘሮ ጥሩዬ ከበደ በከተማው በሚከናወኑ የልማት ስራዎች ተሳትፏቸውን እንደሚያጠናክሩ ተናግረዋል ።
በሲዳማ ክልል የሆኮ ወረዳ ነዋሪዎች በአማራጭ የኃይል አቅርቦት ሥራዎች ተጠቃሚ ሆነዋል
Jun 24, 2026 180
ሀዋሳ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ):-በሲዳማ ክልል የሆኮ ወረዳ ነዋሪዎች በመንግስት በተከናወኑ አማራጭ የኃይል አቅርቦት ሥራዎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናገሩ። በወረዳው በሆዲ ቦኩ ከተማ ከፀሐይ ሀይል 525 ኪሎ ዋት የሚያመነጨው የሆዲ ቦኩ ሚኒ ግሪድ የፀሐይ ሀይል ማመንጫ ፕሮጀክት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል።   መንግስት የኤሌክትሪክ ሀይል አገልግሎት ባለተዳረሰባቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች የሶላር ሚኒ ግሪድ ሃይል ልማትን በማስፋፋት ዜጎች የአማራጭ ሀይል ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየሰራ ነው። በሲዳማ ክልል የሆኮ ወረዳ ነዋሪዎችም በቅርቡ ተገንብቶ ለአገልግሎት በበቃው የሆዲ ቦኩ ሚኒ ግሪድ የፀሐይ ሀይል ማመንጫ ፕሮጀክት ተጠቃሚ መሆን ጀምረዋል። ኢዜአ በሆኮ ወረዳ ሆዲ ቦኩ ከተማ ካነጋገራቸው ነዋሪዎች መካከል አቶ አሸናፊ ሌንጅሶ እንዳሉት፣ በአካባቢው የኤሌክትሪክ ሀይል አገልግሎት ባለመኖሩ ለተለያዩ ችግሮች ተዳርገው ቆይተዋል።   በአሁኑ ወቅት በፀሐይ ሀይል የሚሰራ አማራጭ ሀይል ማግኘታቸው ኑሯቸውን ከማቅለሉ ባለፈ ማህበራዊ አገልግሎቶችንም በተሻለ ለማግኘት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። አማራጭ የሀይል አቅርቦት መኖሩ በጤና ተቋማት የሚሰጠው የሕክምና አገልግሎት እንዲሻሻል ማድረጉንም ተናግረው፣ ህብረተሰቡ የሀይል ተጠቃሚ እንዲሆን መንግስት ለመኖሪያ ቤት ቆጣሪ በነጻ ማቅረቡንም ተናግረዋል።   ለዘመናት የነበረው የሀይል ጥያቄያቸው በመፈታቱ መደሰታቸውን የገለጹት ደግሞ አቶ ጎሹ ጋኖሌ የተባሉ ነዋሪ ናቸው። በአካባቢያቸው የተገነባው የሀይል ማመንጫ ፕሮጀክት ኑሯቸውን በማቃለል ጉልበትና ጊዜያቸውን ለሥራ በማዋል ሕይወታቸውን ለመለወጥ የተሻለ ዕድል እንደፈጠረላቸውም ተናግረዋል። አካባቢው የሀይል ተጠቃሚ መሆኑ ለንግድ እንቅስቃሴም ሆነ የተለያዩ የሥራ ዕድሎችን በራስ ፈጥሮ ለመስራት ፋይዳው የጎላ መሆኑን አመልክተዋል።   በሆዲ ቦኩ ከተማ የ9ኛ ክፍል ተማሪው ምንጬ ደምሴ በበኩሏ "በመብራት እጦት ለተለያዩ ችግሮች ተዳርገን ቆይተናል፤ ይሁን እንጂ በቅርቡ በተመረቀው የፀሀይ ሀይል ማመንጫ ፕሮጀክት ከጨለማ ሕይወት ወጥተናል" ብላለች። የሀይል አቅርቦቱ ተማሪው በአግባቡ እንዲማር፣ ህብረተሰቡም ዘመናዊ ህይወትን እንዲላመድ እና ለወጣቱም የሥራ ዕድል ፈጠራ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ተናግራለች።   የሲዳማ ክልል ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ልማት ቢሮ ሃላፊ ኢንጂነር ከበደ ጋኖሌ በበኩላቸው በክልሉ የሀይል ተደራሽነትን ለማስፋት በተሰሩ ሥራዎች የዜጎች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች እየተፈቱ ነው። ከዋናው የኤሌክትሪክ መስመር ርቀው የሚገኙ የክልሉ አካባቢዎችን በአማራጭ የሀይል አቅርቦት ተጠቃሚ ለማድረግ ታስቦ ከተጀመሩ አምስት የሀይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች ሁለቱ ተጠናቀዋል ብለዋል። በእዚህም የህዝቡ የሀይል አቅርቦት ጥያቄ እየተመለሰ መምጣቱን ኢንጂነር ከበደ ገልጸው፣ "በሆኮ ወረዳ የተመረቀው የፀሐይ ሀይል ማመንጫ ፕሮጀክት ከ2ሺህ የሚበልጡ አባውራዎችን ተጠቃሚ ያደርጋል" ብለዋል።   በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የፕሮጀክት ፖርትፖሊዮ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ክንፈ ነጋሽ በበኩላቸው የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተደራሽነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ለእዚህም ከዋናው የኤሌክትሪክ መስመር ውጭ በሆኑ አካባቢዎች አማራጭ የፀሐይ ሀይል በማስፋፋት ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በእዚህም በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች 97 ፕሮጀክቶች በግንባታ ሂደት ላይ መሆናቸውንና 43 እንደተጠናቀቁ ገልጸዋል። በእነዚህ አካባቢዎች ዜጎች የሀይል ተጠቃሚ እንዲሆኑ የመኖሪያ ቤት ቆጣሪ በነጻ እየቀረበላቸው መሆኑን የገለጹት አቶ ክንፈ፣ የዜጎችን የሀይል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ጥረቶች በቀጣይም ይጠናከራሉ ብለዋል።
በክልሉ የቱሪዝም ዘርፉን ይበልጥ ለማጎልበት የሚያስችሉ የልማት ስራዎች በስፋት እየተተገበሩ ይገኛሉ 
Jun 24, 2026 169
ሐረር ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል የቱሪዝም ዘርፉን ይበልጥ ለማሳደግና ለማጎልበት የሚያስችሉ የኢንቨስትመንትና የልማት ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ተናገሩ። ርዕሰ መስተዳድሩ ኦርዲን በድሪ በሐረር ከተማ በግንባታ ላይ ያሉ የተለያዩ ኢንቨስትመንቶችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል። የሐረሪ ክልል በተለይም ጥንታዊቷ የጀጎል ግንብ የዓለም ቅርስነት ከተመዘገበበት ጊዜ ጀምሮ በኢትዮጵያ ቀዳሚ ከሆኑ የባህልና የታሪክ ቱሪዝም መዳረሻዎች አንዷ ናት። ከተማዋ ያላት ልዩ የእስልምና ታሪክ ቅርሶች፣ የሀረሪ ባህላዊ ቤቶች፣ የጅብ መመገብ ልማድ እንዲሁም የህዝቡ የአብሮነትና የሙዚቃ ባህል በየዓመቱ በርካታ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር ጎብኝዎችን ይስባል።   የክልሉ መንግስትም በቅርብ ዓመታት ውስጥ በርካታ የሪፎርም እና የልማት ስራዎችን በማከናወን ላይ ሲሆን፥ በተለይም የቱሪዝም ዘርፉን በግል ባለሀብቱ ኢንቨስትመንት እገዛ ለማሳደግ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል። ርዕሰ መስተዳድሩ በወቅቱ እንዳሉት የክልሉ መንግስት በኢንቨስትመንት አማራጮች ላይ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች አስፈላጊውን ማበረታቻና ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠሩን አንስተዋል። በክልሉ ለኢንቨስትመንት ዘርፍ ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር በተደረገው የተቀናጀ ጥረትም አመርቂ ለውጥ መመዝገቡን ርዕሰ መስተዳድሩ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በከተማው በግል ባለሀብቶች እየተገነቡ ያሉ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶችም አበረታች ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ገልጸው፤ የግንባታ ስራዎቹም በታቀደላቸው የጊዜ ሰሌዳ እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። የልማት ፕሮጀክቶቹ የክልሉን የቱሪዝም አቅም ለማሳደግና ለዜጎች የሚሆን የሥራ ዕድልን በስፋት ለመፍጠር ያላቸው ፋይዳም ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመዋል።   በኢንቨስትመንት አማራጮች ላይ ተሰማርተው አበረታች አፈጻጸም እያሳዩ ላሉ ባለሀብቶች፣ የክልሉ መንግስት የሚያደርገውን ዘርፈ ብዙ ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ርዕሰ መስተዳድሩ አረጋግጠዋል። ባለሀብቶቹም የጀመሩትን የግንባታ ስራ በፍጥነትና በጥራት አጠናቀው ለአገልግሎት ማብቃት እንዳለባቸውም ርዕሰ መስተዳድሩ አሳስበዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ ባካሄዱት በዚህ ምልከታ ላይ የክልሉ ኢንቨስትመንት ቦርድ አባላትን ጨምሮ ሌሎች የሥራ ኃላፊዎች መታደማቸው ታውቋል።
በኦሮሚያ ክልል በመኸር እርሻ እስካሁን ከ4 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል  
Jun 24, 2026 269
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 17/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በመኸር እርሻው እስካሁን ከ4 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ እንዳሻው ጀማነህ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በመኸር እርሻ 11 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር መሬትን በኩታገጠም በማልማት ከ380 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዶ እየተሰራ ነው።   በክልሉ እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴ ከ9 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ታርሶ ለዘር መዘጋጀቱን ተናግረዋል። በዘንድሮው የመኸር እርሻ ወቅት በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች በዋናነት የጥራጥሬ እና የሰብል ዘር ዓይነቶች እየተዘሩ መሆኑን ገልጸዋል። ታርሶ ለዘር ከተዘጋጀው መሬት ውስጥ እስካሁን 4 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታሩ በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ተሸፍኗል ብለዋል። ለመኸር እርሻ ከተዘጋጀው መሬት ውስጥ እስካሁን ከ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ የሚሆነው በትራክተር ታግዞ መታረሱን ጠቁመዋል። በክልሉ ለመኸር እርሻ ሥራው ከ14 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ለማቅረብ ታቅዶ፣ እስካሁን ከ8 ነጥብ 7 ሚሊዮን በላይ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ሕብረት ሥራ ማህበራትና በዩኒየኖች ጋር መድረሱን ገልጸዋል።   ለማህበራቱና ለዩኒየኖቹ ከደረሰው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ ከ4 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ለአርሶ አደሩ መከፋፈሉን አንስተዋል። እንዲሁም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ይረዳ ዘንድ የተለያዩ ምርጥ ዘሮች ለአርሶ አደሮቹ መቅረባቸውን አክለዋል። በክልሉ በአሁኑ ወቅት ያለው የዝናብ ሁኔታ መልካም በመሆኑ አርሶ አደሩ ያለውን ምቹ ሁኔታ በአግባቡ በመጠቀም ከፍተኛ ርብርብ እያደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በክልሉ በመኸር እርሻው የታቀደውን ምርት ለማግኘት በየደረጃው ያሉ አመራሮችና ባለሙያዎች ለአርሶ አደሩ ድጋፍና ክትትል እያደረጉላቸው ይገኛሉ ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም