ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በአማራ ክልል የሰላም አማራጭን የተቀበሉ የቀድሞ የመንግሥት ሠራተኞች ወደ ሥራቸው እንዲመለሱ ተወሰነ
Feb 26, 2026 77
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ የሰላም አማራጭ ተቀብለው የተመለሱ እና በተለያዩ የመንግሥት መዋቅር ስር ሲያገለግሉ የነበሩ የቀድሞው የመንግሥት ሰራተኞች ወደ መንግሥት ስራቸው እንዲመለሱ የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት መስተዳድር ምክር ቤት ውሳኔ አሳልፏል። የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት መስተዳድር ምክር ቤት ባካሔደው 6ኛ ዙር፣ 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 8ኛ መደበኛ ስብሰባው የሰላም አማራጭን ተቀብለው በተመለሱና ቀደም ሲል በተለያዩ የመንግሥት መዋቅሮች ሲያገለግሉ በነበሩ ሠራተኞች ላይ ውሳኔ አሳልፏል።   የክልሉ መንግሥት ሰላምን ለማጽናትና ልማትን ለማረጋገጥ ባለው ጽኑ ቁርጠኝነት፣ ታጥቀው ለሚንቀሳቀሱ አካላት በተደጋጋሚ የሰላም ጥሪ ሲያቀርብ መቆየቱ ይታወሳል። በዚህም መሠረት በመንግሥት ጥሪ፣ በድርድርና በውይይት የሰላም አማራጭን መርጠው የተመለሱና የተሃድሶ ሥልጠና የወሰዱ የቀድሞ የመንግሥት ሠራተኞች ወደ መደበኛ ሥራቸው እንዲመለሱ ምክር ቤቱ ወስኗል። ይህ ውሳኔ የክልሉ መንግሥት ልዩነቶችን በሰለጠነ መንገድ ለመፍታትና ለዘላቂ ሰላም መረጋገጥ ያለውን ዝግጁነት የሚያሳይ መሆኑ ተገልጿል። በቀጣይም ለክልሉ ዕድገትና አንድነት መሰል የሰላም ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተመላክቷል።
በክልሉ መንግሥት ተገንብተዉ ለአገልግሎት ክፍት የተደረጉ ፕሮጀክቶች ተጠቃሚነታችንን የሚያሳድጉ ናቸው- ነዋሪዎች
Feb 26, 2026 60
ሆሳዕና፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ) ፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል መንግሥት ተገንብተው ለአገልግሎት ክፍት የተደረጉ ፕሮጀክቶች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው መሆናቸውን የሀዲያ ዞን ነዋሪዎች ገለፁ፡፡ በዞኑ በተለያዩ መዋቅሮች የተገነቡ የመንገድ፣ የመስኖና የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ተደርገዋል፡፡   የዞኑ ነዋሪዎች በዚህ ወቅት እንደገለጹት በክልሉ መንግሥት ተገንብተው ለአገልግሎት ክፍት የተደረጉ ፕሮጀክቶች የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ናቸው፡፡ አርሶ አደር ከድር ዋበላ በሀድያ ዞን ሻሸጎ ወረዳ ዶኢሻ ከተማ ነዋሪ ሲሆኑ በአካባቢው ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት የተደረገው የመስኖ ፕሮጀክት ምርትና ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እንደሚረዳቸው ገልጸዋል።   በተለይም በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የነበረውን የእርሻ ስራ እስከ ሶስት ጊዜ በማሳደግ የተሻለ ምርት ለማግኝት እንደሚረዳቸውም ነው የገለጹት። በሌሞ ወረዳ አምቢቾ ጎዴ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ሸጋ ደሳለኝ በበኩላቸው፤ ፕሮጀክቱ መመረቁ ንጹሕ የመጠጥ ውሃ ለማግኘት ይጓዙ የነበረውን ረጅም ርቀት እንዳስቀረላቸው ነው የሚናገሩት።   የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደገለፁት የክልሉ መንግስት የህዝቡን ጥያቄ መሰረት ያደረጉ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶችን ተግባራዊ ማድረጉን ይቀጥላል ። በክልሉ ፈጣን እድገትን ለማረጋገጥ ከማህበረሰቡ ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝም ነው የተናገሩት።   በክልሉ የተጀመረውን ሁሉን አቀፍ ልማት አጠናክሮ በማስቀጠል የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የተጀመረው ትብብር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው ያብራሩት። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ መሀመድ ኑርዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው በሃዲያ ዞን ከ250 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው ፕሮጀክቶች መመረቃቸውን ገልፀዋል፡፡   ፕሮጀክቶቹ የመንገድ፣ የአነስተኛ መስኖና የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ሲሆኑ የማህበረሰቡን ጥያቄ ደረጃ በደረጃ የመለሱና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል፡፡  
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን በሚደረገው ጥረት አበረታች ውጤት ተገኝቷል
Feb 26, 2026 143
አሶሳ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን በሚደረገው ጥረት አበረታች ውጤት መገኘቱን የክልሉ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ። በክልሉ የሰብአዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን በኮሚሽኑ አማካኝነት በአቡራሞ ወረዳ የለማ ሰብል ተሰብስቧል። የክልሉ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሐመድ አብዱላዚዝ፣ እንዳሉት በ2016/17 የምርት ዘመን ለሰብዓዊ ድጋፍ ታስቦ በውስን አካባቢዎች የተጀመረው የሰብል ልማት አበረታች ውጤት ተገኝቶበታል።   በዘንድሮው ዓመት በክልሉ 1 ሺህ 804 ሄክታር ማሳ ላይ በለማው የበቆሎ፣ ማሽላ፣ አኩሪ አተር እና ሌሎች ሰብሎች እስከአሁን ድረስ 36 ሺህ 211 ኩንታል ምርት መገኘቱን ገልጸዋል። በምርት ዘመኑ ከ43 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ መሆኑን ገልፀው፥ የምርት አሰባሰብ ሂደቱ ሲጠናቀቅ ዕቅዱ ሙሉ ለሙሉ እንደሚሳካ ጠቁመዋል። የክልሉ አደጋ ስጋትና ስራ አመራር ኮሚሽን በራሱ አቅም በክልሉ አቡራሞ እና ሆሞሻ ወረዳዎች ላይ ካለማው ማሳ 2 ሺህ 200 በላይ ኩንታል ምርት መሰብሰቡንም ተናግረዋል። የተሰበሰበው ምርት የውጪ እርዳታን በራስ አቅም ለመሸፈን የሚያግዝና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ጉልህ ድርሻ እንዳለውም ተናግረዋል። ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ለማሳካት መንግስት በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን የተናገሩት ኮሚሽነሩ ምርቱም ለታለመለት ዓላማ ብቻ እንዲውል ይደረጋል ብለዋል። በቀጣይም በክልሉ የሚገኙ ሰፋፊ የእርሻ ማሳዎችን በማስፋት ምርታማነትን ለማሳደግ እና ከተረጂነት ለመላቀቅ የተያዘውን የዜሮ ፕርሰንት ሀገራዊ ግብ ለማሳካት በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል ።  
በአማራ ክልል የንጹህ መጠጥ ውሃ ሽፋንን የሚያሳድጉ የውሃ ተቋማት ግንባታ ተጠናክሮ ቀጥሏል
Feb 26, 2026 102
ባህር ዳር ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የንጹህ መጠጥ ውሃ ሽፋንን የሚያሳድጉ የውሃ ተቋማት ግንባታ ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ገለጸ። በክልሉ በተከናወኑ የውሃ ተቋማት ግንባታና ጥገና ከ170 ሺህ በላይ ዜጎች የንጹሕ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ ሆነዋል። የውሃ ተቋማቱ በተለይም በገጠርና በከተማ የሚገኙ እናቶችንና ሕፃናትን ከእንግልት መታደግ ችለዋል። የአማራ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ጥላሁን ሽመልስ ለኢዜአ እንዳሉት በገጠርና ከተሞች የንፁህ መጠጥ ውሃ ለህብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ከ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ተይዞ እየተከናወነ ነው። በተያዘው በጀት ዓመት ከሁለት ሺህ በላይ አነስተኛ የውሃ ተቋማትን ለመገንባት ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን አመልክተዋል። ባለፉት ሰባት ወራት ከሁለት ሺህ በላይ የውሃ ተቋማትን ወደ ግንባታ ማስገባት የተቻለ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ የ306ቱን በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ማብቃት መቻሉን አብራርተዋል። እንዲሁም የ55 ከፍተኛ የውሃ ተቋማት ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፣ ከእነዚህ ውስጥ 17 የሚሆኑት ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል ነው ያሉት። የውሃ ተቋማቱ ከ170 ሺህ በላይ ዜጎችን የንፁህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ ማድረግ መቻላቸውን ገልጸው የክልሉን የንጹህ መጠጥ ውሃ ሽፋን እየተከናወኑ ያሉ ግንባታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። እንደ ኃላፊው ገለጻ፣ በክልሉ ለብልሽት የተዳረጉ ከ13 ሺህ በላይ የውሃ ተቋማት በሕብረተሰብ ተሳትፎ ተጠግነው ለአገልግሎት በቅተዋል። የውሃ ተቋማቱን ዘላቂነት ለማረጋገጥም አደረጃጀት በመፍጠር የጥበቃና የእንክብካቤ ስራ እየተሰራ እንደሆነ አመልክተው በቀሪ ወራትም ግንባታቸው የተጀመሩ የውሃ ተቋማትን በማጠናቀቅ ለአገልግሎት እንዲበቁ በቅንጅት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ምዕራብ በለሳ ወረዳ ነዋሪ ማሪቱ በላይነህ በአቅራቢያቸው የንፁህ መጠጥ ውሃ ባለመኖሩ ውሃ ፍለጋ ረጅም መንገድ በመጓዝ እንግልት ይደርስባቸው እንደነበር አስታውሰዋል። በአቅራቢያቸው ተገንብቶ ለአገልግሎት የበቃው የውሃ ፕሮጀክት የቀደመ ችግራቸውን በመፍታቱ የንፁህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ መሆን እንደቻሉ ተናግረዋል። በዚህ ዓመት ተገንብቶ አገልግሎት የጀመረው የጋብላ ውሀ ፕሮጀክት የንጹህ መጠጥ ውሃ ችግራችንን የፈታ ነው ያሉት ደግሞ በምዕራብ ጎንደር ዞን ምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ ጋብላ ከተማ ነዋሪ ግርማ ደግሰው ናቸው። ሌላኛዋ በዚሁ ወረዳ ጠረፍ ወርቅ ቀበሌ ነዋሪ ፋሲካ አንተነህ እንዳሉት፤ በፀሐይ ብርሃን የሚሰራ የንፁህ መጠጥ ውሃ ተቋም ለአገልግሎት መብቃቱ ውሃ ለማግኘት ያደርጉት የነበረውን ረጅም ጉዞ እንዳስቀረላቸው ገልፀዋል። በክልሉ አሁን ያለው የንጹህ መጠጥ ውሃ ሽፋን ከ77 በመቶ በላይ የደረሰ ሲሆን ይህን ለማሳደግ የተለያዩ የውሃ ተቋማት ግንባታ ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ነው።    
በቱሪዝም ዘርፍ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትና ተወዳዳሪነትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት ተመዝግቧል
Feb 26, 2026 125
አርባ ምንጭ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ የቱሪዝም ዘርፉን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትና ተወዳዳሪነትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት መመዝገቡን የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሣ አስታወቁ። የቱሪዝም ሚኒስቴር የ2018 በጀት ዓመት የዘርፉ የግማሽ ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ ሚኒስትር ሰላማዊት ካሣ እንደተናገሩት የቱሪዝም ዘርፍ ለ10 ዓመት የሀገሪቱ የልማት ዕቅድ ስኬት ወሳኝ ድርሻ ያለው በመሆኑ ሚኒስቴሩ የመካከለኛ ዘመን ዕቅድ ነድፎ እየሠራ ይገኛል ብለዋል። በሀገሪቱ ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ የቱሪዝም ፀጋዎችን በመጠበቅ፣ በማልማትና የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማስፋፋት የዘርፉን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተጀመሩ የገበታ ለሀገርና ለትውልድ ፕሮጀክቶች በአዳዲስ እይታ በዘርፉ ላይ አዲስ ምዕራፍ የከፈቱ ናቸው ብለዋል።   እንደ ሀገር የቱሪዝም ዘርፍ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ አዳዲስ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማትና ነባሮቹን በማጠናከር ለጎብኚዎች ክፍት መደረጉንና በዚህም ውጤት መገኘቱን ጠቅሰዋል። በርካታ ባህላዊና ተፈጥሯዊ ሀብቶችን በዩኔስኮ ለማስመዝገብ በተደረጉ ጥረቶች ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ጠቅሰው ይህን አጠናክሮ ለማስቀጠልም ይሰራል ብለዋል። በፈረንጆች 2025 በቱሪዝም ዘርፍ 15 በመቶ ዕድገት መመዝገቡን አስታውሰው፣ ለዚህም የመገናኛ ብዙሃን፣ የግሉ ዘርፍ፣ የልማት አጋሮችና ሌሎች ድርሻቸው ጉልህ እንደነበር ተናግረዋል። በቀሪ ወራትም በየደረጃው ያሉ ተቋማትን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ለማጠናከር፣ ብቁ አመራሮችና ባለሙያዎችን ለመፍጠርና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት በትኩረት ይሠራል ነው ያሉት። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በበኩላቸው ቱሪዝም ከብዝሃ ዘርፍ የኢኮኖሚ አምዶች መካከል ለብልጽግና ጉዞ ስኬት አይተኬ ሚና እንዳለው አንስተዋል። በክልሉም ሰፊ የቱሪዝም አቅም እንዳለ ጠቁመው፤ በተለይ የረጅም ጊዜ የታሪክ፣ የድንቅ ባህል፣ የተፈጥሮ ሀብት እንዲሁም የብዝሃነት ፀጋ ባለቤት መሆኑ ለዘርፉ ዕድገት ትልቅ አቅም ነው ብለዋል። ከክልሉ በዩኔስኮ የተመዘገቡ ቅርሶች፣ ብሔራዊ ፓርኮች እንዲሁም ባህላዊ፣ ተፈጥሯዊና ሃይማኖታዊ የቱሪዝም ሀብቶች ለሀገሪቱ ዕድገት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑንም ጠቅሰዋል። የመስህብ ስፍራዎቹን በማልማት፣ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን በማስፋፋትና ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር የዘርፉን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማላቅ የክልሉ መንግስት በልዩ ትኩረት እየሠራ ይገኛል ነው ያሉት። አርባ ምንጭ ከተማ በቱሪዝም ሀብቷና በሰላም እሴቷ የደመቀች በመሆኗ ለቱሪዝም ዕድገት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላት የገለጹት ደግሞ የከተማዋ ከንቲ መስፍን መንዛ(ዶ/ር) ናቸው። በከተማዋ እየተገነባ ያለው የገበታ ለትውልድ ኮንፍረንስ ሪዞርት ለዘርፉ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ጠቅሰው፣ የመስህብ ስፍራዎችን በማልማት የዘርፉን ኢኮኖሚያዊ አበርክቶ ከፍ ለማድረግ እየተሠራ ነው ብለዋል። ለሁለት ቀናት በሚቆየው በዚህ መድረክ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የንግድና ቱሪዝም ቋሚ ኮሚቴ አባላትን ጨምሮ ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደር የዘርፉ ተጠሪዎች በመሳተፍ ላይ ናቸው።
በክልሉ የመንገድ መሰረተ ልማት ተደራሽነትን የማስፋት ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Feb 26, 2026 109
ሆሳዕና ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የመንገድ መሰረተ ልማት ተደራሽነትን የማስፋት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በክልሉ የመንገዶች አስተዳደር የሆሳዕና ዲስትሪክት የተገነባው የማሬ -አቡና -መሰና -ጃጁራ የ30 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል፡፡   ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የክልሉ መንግሥት የህዝብ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ ተግባራትን እውን የማድረግ ስራን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በርካታ ፕሮጀክቶች ወደ ልማት እንዲገቡ ይደረጋል በተለይ የመንገድ መሰረተ ልማት ተደራሽነትን የማስፋት ተግባራትን አጠናክሮ በማስቀጠል ፈጣን እድገትን ለማረጋገጥ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።   ለአገልግሎት ክፍት የተደረገው መንገድ ኢኮኖሚውን ለማነቃቃት ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ በመሆኑ የአካባቢው ማህበረሰብ መሰረተ ልማቱን በአግባቡ ሊጠቀምበት ይገባል ብለዋል፡፡ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የመንገድ ልማትና ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ መሀመድ ኑርዬ በበኩላቸው፤ ዛሬ የተመረቀው የ30 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ በርካታ እድሎችን ይዞ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡   የተገነባው መንገድ ከምባታ ዞንን ከሀዲያ ዞን ጋር በሚያገናኙ በ11 ቀበሌያት በኩል በማለፍ ወደ 262 ሺህ የሚጠጋ ቁጥር ያላቸው የማህበረሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል፡፡ የመንገዱ ግንባታ ከ 173 ሚሊዮን 963 ሺህ ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበትም ገልፀዋል፡፡   የመንገድ መሰረተ ልማቱ መጠናቀቅ በአካባቢው የሚመረቱ የግብርና ምርቶችን በቀላሉ ለገበያ ለማቅረብ እንደሚረዳ የተናገሩት ደግሞ የሀዲያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቲዎስ አኒዮ ናቸው፡፡   አካባቢው በግብርናው ዘርፍ ያለውን እምቅ አቅም ለመጠቀም የመንገዱ ግንባታ ሰፊ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ነው የተናገሩት። በአካባቢው በነበረው የመንገድ መሰረተ ልማት ችግር ያመረቱትን ምርት ለገበያ ለማቅረብ ይቸገሩ እንደነበር የተናገሩት ደግሞ በሀዲያ ዞን በሶሮ ወረዳ የ2ኛ በናራ ቀበሌ ነዋሪው አቶ ገበየሁ ሐይሉ ናቸው፡፡   ወላድ እናቶችንና የጤና እክል የገጠማቸውን የማህበረሰብ ክፍሎች ወደ ጤና ተቋም ለማድረስ ይገጥም የነበረውን ችግር ከማቃለል አንፃርም የመንገዱ ግንባታ ሰፊ አስተዋጽኦ እንደሚኖሩው ነው የጠቀሱት። በመርሐ ግብሩ የክልልና የዞን ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች እንዲሁም የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የገበያ ትስስርና ዘላቂ የግብዓት አቅርቦትን እየፈጠረ ነው
Feb 26, 2026 117
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለምርቶቻቸው የገበያ ትስስርና ዘላቂ የግብዓት አቅርቦት እየፈጠረላቸው መሆኑን አምራቾች ገለጹ። የኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት በበኩሉ፥ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተቋማዊ ቅንጅትን በማጠናከር በዘርፉ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን የሚፈታ ምህዳር መፍጠሩን አስታውቋል። መንግሥት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ዕድገት ለማፋጠን የኢንዱስትሪውን ዘርፍ አንዱ የብዝኃ ዕድገት ምሰሶ አድርጓል። በተለይም በማምረቻው ዘርፍ የተሰማሩ አምራቾች በተኪ ምርት ላይ እንዲያተኩሩና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን እንዲያሳድጉ መንግስት የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገ ይገኛል። ለዚህም በዘርፉ ያሉ መዋቅራዊ ማነቆዎችን በመፍታት እመርታ ለማምጣት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ወደ ትግበራ ገብቶ ከፍተኛ ውጤት እያስገኘ ነው ኢዜአ ያነጋገራቸው አምራቾች እንደገለጹት፣ ንቅናቄው የገበያ ትስስርን ለመፍጠር፣ የግብዓት አቅርቦትን ለማመቻቸትና ምርቶቻቸውን ለማስተዋወቅ ምቹ ሁኔታ ፈጥሮላቸዋል። የአሸናፊና ይርጋለም ብረታብረት እና ኢንጂነሪንግ ህብረት ሽርክና ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ አሸናፊ ኃይለጊዮርጊስ፥ ማህበሩ ከውጭ የሚገቡ የእንጨት መሰንጠቂያ ማሽኖችን በሀገር ውስጥ ምርት ለመተካት እየሰራ ነው ብለዋል። ንቅናቄው አምራቾችን ከመንግሥትና ከሌሎች አጋር አካላት ጋር በማገናኘት የግብዓት አቅርቦት ችግሮች እንዲፈቱ መንገድ መክፈቱን ጠቅሰዋል።   የዌላንድ ኢንዱስትሪ የፕሮጀክት ማናጀር ሊዲያ ተስፋዬ፥ ንቅናቄው ለኤሌክትሪክ ገጠማ የሚውሉ የፕላስቲክ ምርቶቻቸውን በቀላሉ ለተጠቃሚዎች ለማድረስ እንደረዳቸው አንስተዋል።   በፋሲል ታሪኩ የቤትና ቢሮ እቃዎች ማምረቻ ባለሙያ የሆኑት ወንድምነህ አብየ፣ በሀገር ውስጥ የተመረቱ የእንጨት ውጤቶች ማምረቻ ማሽነሪዎች ማግኘት መቻላቸው ለስራቸው ትልቅ እገዛ ማድረጉን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ሚልኬሳ ጃገማ(ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ንቅናቄው ከመጀመሩ በፊት የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም በግብዓት፣ በፋይናንስና በአሰራር ጉድለቶች ምክንያት ዝቅተኛ ነበር። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተቋማዊ ቅንጅትን በማጠናከር በዘርፉ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን የሚፈታ ምህዳር ፈጥሯል ብለዋል። የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ወደ 66 ነጥብ 3 በመቶ ማደጉን፣ ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ 3 ነጥብ 4 ቢሊየን ዶላር የሚገመቱ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የውጭ ምንዛሬ ማዳን መቻሉን ጠቅሰዋል።
በዞኑ ለዘንድሮ የበልግ እርሻ የሚውል ከ892 ሺህ ኩንታል በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ተዘጋጅቷል 
Feb 26, 2026 68
ነገሌ ቦረና ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በምስራቅ ቦረና ዞን ለዘንድሮ የበልግ እርሻ የሚውል ከ892 ሺህ ኩንታል በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ መዘጋጀቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ወጪን ለመቀነስ አግዞናል- በምሥራቅ ጎጃም አርሶ አደሮች የጽህፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ ኩልሌ ሸና እንዳሉት፤ ከፊል አርብቶ አደሩ ለተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅት ትኩረት ሰጥቶ እንዲሰራ ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ ይገኛል። በመሆኑም ለዘንድሮ የበልግ እርሻ የሚውል አንድ ሚሊዮን ኩንታል የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ነው የተናገሩት። በዞኑ በሁሉም ወረዳዎች እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴ ከፊል አርብቶ አደሮችን በማሳተፍ 892 ሺህ 934 ኩንታል የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማዘጋጀት መቻሉን አስረድተዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያው በዘንድሮው ዓመት በበልግ እርሻ ለሚለማው ከ30 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በግብዓትነት እንደሚውል ገልጸዋል።   በዞኑ በስፋት የሚካሄደው የእንስሳት እርባታ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ጠቅሰው ይህን አቅም ለመጠቀም ትኩረት መሰጠቱን አስታውቀዋል። ዝግጅቱ ከፋብሪካ የሚገኘውን ማዳበሪያ ወጪን ከመቀነስ ባለፈ የአፈር ለምነትን በመጠበቅ እስከ ሶስት ዓመት ከፍተኛ ምርት ለማግኘት እንደሚያስችል አስረድተዋል። ከተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅቱ በተጨማሪ ለበልግ እርሻ የሚውል ከ50 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ወደ ዞኑ ደርሶ ስርጭት እየተካሄደ መሆኑን አክለዋል። የበልግ እርሻ ስራን ለማቀላጠፍ በርካታ የእርሻ ትራክተሮች ወደ አካባቢው እየገቡ መሆኑንም ጠቁመዋል። በዞኑ በበልግ እርሻ ከሚለማው 178 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ከ3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱንም አንስተዋል። ባለፈው መኸር ወቅት ያለሙት የስንዴ ሰብል በዝናብ እጥረትና በግብአት አጠቃቀም ጉድለት ውጤታማ ባለመሆኑ እሱን ለማካካስ እየሰራሁ ነው ያሉት በዞኑ ሊበን ወረዳ የመኤሳ ዳሎሬ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር እስማኤል ማሊማ ናቸው።   ለዚህም የተፈጥሮ ማዳበሪያ በማዘጋጀት ጥቅም ላይ ለማዋል እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ ሊበን ወረዳ የጎቢቻ ቀበሌ ነዋሪ አብዲ ኑር፤ ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን በሰብል ልማት በመሳተፍ የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥ መቻላቸውን ተናግረዋል።   በዘንድሮ ዓመትም የተፈጥሮና የፋብሪካ ማዳበሪያ በማመጣጠን እና የተሻሻለ የግብርና አሰራር በመከተል ከበልግ አዝመራ የተሻለ ምርት ለመሰብሰብ ዝግጅት ማድረጋቸውን አስታውቀዋል። በምስራቅ ቦረና ዞን ከመጋቢት 15 እስከ ሚያዝያ መጨረሻ የዝናብና የበልግ አዝመራ ወቅት ነው።
በጋሞ ዞን በበልግ አዝመራ ከ125 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ዝግጅት እየተደረገ ነው
Feb 26, 2026 98
አርባ ምንጭ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በጋሞ ዞን በበልግ አዝመራ ከ125 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት ምርታማነትን ለማሳደግ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የዞኑ አርሶ አደሮች በበኩላቸው በበልግ አዝመራ የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀማቸውን በማሳደግና አስፈላጊውን ግብዓት በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በጉራጌ ዞን በበጋ መስኖ ወደ 27 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቷል የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ሃላፊ አቶ ወርቅነህ ካልሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በበልግ አዝመራ ምርታማነትን ለማሳደግ ከማሳ ልየታ ጀምሮ በግብአት አቅርቦት በቂ ዝግጅት ተደርጓል። በበልግ አዝመራ ከ125 ሺህ 897 ሄክታር በላይ መሬት በአዝርዕት፣ በሆርቲካልቸርና በዓመታዊ ሰብሎች እንደሚሸፈን ገልጸው፣ በዚህም ከ17 ሚሊዮን 843 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዷል ብለዋል።   በልማቱም ምርታማነትን ለማሳደግ በተለይ በሞዴል አርሶ አደሮችና በግብርና ሠርቶ ማሳያዎች የክህሎት ማሳደጊያ ስልጠና ለአርሶ አደሩ መሰጠቱን ጠቁመዋል። በበልግ ከሚለማው መሬት ከ75ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት በኩታ ገጠም እንደሚለማ ጠቁመው፣ ለልማቱም ከ156ሺህ ሄክታር በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ ቀርቧል ብለዋል፡፡ እንደ አቶ ወርቅነህ ገለጻ፤ በአርሶ አደሮችና በባለሀብቶች እጅ ያሉ ከ84 በላይ ማረሻ ትራክተሮችን በማቀናጀት ከ52 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ በሜካናይዜሽን ይለማል። በዞኑ በምዕራብ አባያ ወረዳ ፉራ ቀበሌ ሞዴል አርሶ አደር ሮባ ሎላሶ በበኩላቸው፤ በበልግ አዝመራ ምርታማነታቸውን ለማሳደግ የሚያስችሉ የክህሎት ስልጠና እንዳገኙ ገልጸዋል። አስር ሄክታር መሬታቸውን በትራክተር ታግዘው ደጋግመው በማረስ ማለስለሳቸውን ገልጸው በአሁኑ ወቅትም ማሾ፣ በቆሎ፣ ሱፍና ጤፍ ለመዝራት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ለልማቱ በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው መሆኑን ገልጸው፣ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግም አስፈላጊ ግብአቶችን በመጠቀም ልማቱን እንደሚያከናውኑ አስታውቀዋል። በአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ የጫኖ ጫልባ ቀበሌ አርሶ አደር አለሙ ማሜጫ ፣ የግብርና ልማት ሥራቸው በምግብ እህል የቤተሰባቸውን ፍላጎት ከማሟላት ባለፈ ከምርት ሽያጩ ሀብት ለማፍራት መቻላቸውን ተናግረዋል። በበልግ አዝመራ አስፈላጊውን ግብአትና የግብርና ቴክኖሎጂ በመጠቀም የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ ጠንክረው እየሠሩ መሆኑንም ገልጸዋል።
በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ ያለፉት ወራት 668 የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ወደ ሥራ ገብተዋል
Feb 26, 2026 64
አዳማ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ ያለፉት ወራት የመጠጥ ውሃ ተደራሽነትን በማስፋት የህዝብን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተሰራው ሥራ 668 የውሃ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ወደ ሥራ እንደገቡ የክልሉ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ አስታወቀ። የቢሮ ሃላፊዋ ኢንጂነር ሚሊዮን በቀለ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ የንጹህ መጠጥ ውሃ ተደራሽነትን በማስፋት የህዝብን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። በዚህም አዳዲስ የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶችን ከመገንባት ባለፈ በተለያዩ ምክንያቶች ተበላሽተው የነበሩ የውሃ ፕሮጀክቶችን የመጠገን ሥራ መከናወናቸውን ጠቁመዋል።   በበጀት ዓመቱ ግማሽ ዓመትም 375ሺህ ህዝብ ተጠቃሚ ያደረጉ 668 የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት መብቃታቸውን ገልጸዋል። በተለያዩ ምክንያቶች ተበላሽተው ከአገልግሎት ውጭ የነበሩ 1ሺህ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶችንም በመጠገን የተቋረጠውን አገልግሎት ዳግም ማስጀመር ተችሏል ብለዋል። ለብዙ ጊዜ ግንባታቸው የተጓተተና የህዝብ ቅሬታ ምንጭ የሆኑ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶችን ግንባታ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ለማብቃት እየተሰራ መሆኑንም ኢንጂነር ሚሊዮን አመልክተዋል። እስካሁንም የባሌ ሮቤ ከተማ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ግንባታ መጠናቀቁን ገልጸው በአሁኑ ወቅት ፕሮጀክቱን ከነባር መስመሮች ጋር የማገናኘት ሥራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።   በተመሳሳይ የወሊሶ ከተማ የውሃ ፕሮጀክት ግንባታና የመስመር ዝርጋታ ከሁለት ቀበሌዎች በስተቀር መጠናቀቁን ጠቁመው የሞጆ አዳማ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክትም ተጠናቆ በከፊል አገልግሎት መስጠት መጀመሩን ገልጸዋል። በቀጣይም አፈጻጸማቸው ከ85 በመቶ በላይ የደረሱ ትላልቅ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶችን አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በቀጣይ የክትትልና ቁጥጥር ሥራን በማጠናከር በግንባታ ሂደት ላይ ያሉ የውሃ ፕሮጀክቶችን ሙሉ ለሙሉ አጠናቀን ለአገልግሎት ለማብቃት የተጀመረው ርብርብ ይጠናከራል ብለዋል።
ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ግብ እንዲሳካ የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች ትገኛለች
Feb 26, 2026 60
ድሬዳዋ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ግብ እንዲሳካ የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች መሆኑን በድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሃብት መምህርና ተመራማሪ ዘሪሁን ተምሳስ(ዶ/ር) ገለፁ። በድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሃብት መምህርና የዘርፉ ተመራማሪ ዘሪሁን ተምሳስ(ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ኢትዮጵያ ከወዲሁ እያከናወነች የምትገኘው ዘርፈ ብዙ የልማት እንቅስቃሴዎች ተጨባጭ ለውጥ እያመጡ ነው ብለዋል።   ለአብነትም ባለፉት ዓመታት በማምረቻው ዘርፍ እየተመዘገቡ የሚገኙ ውጤታማ ስራዎች የህብረቱን የኢንዱስትሪ መር ኢኮኖሚ ሽግግር ማሳካት የሚያስቻሉ መሆናቸውን አንስተዋል። ግዙፍ የውጭ ሀገራት ኢንቨስተሮች በተለያዩ ከተሞች በተገነቡ ልዩ የኢኮኖሚ ዞኖችና የኢንዱስትሪ ፓርኮች እያከናወኑ የሚገኙትን ልማቶችን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ሌላው ለህብረቱ አጀንዳዎች መሳካት አስተማማኝ መሠረትና መደላደል እየጣለች መሆኗን ከሚያረጋግጡ ተግባራት መካከል በግብርናው በተለይም በስንዴ ልማት ላይ የተገኘውን ውጤት አንስተዋል። ኢትዮጵያ በዲጂታል ትስስርና በመሠረተ ልማት አስደናቂ ሥራ እያከናወነች ነው ይህም የአፍሪካ ህብረት ሀገራት ያላቸውን ፀጋና ዕውቀት ተጠቅመው የምግብ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥ ጉዞ ማሳካት እንደሚችሉ ትልቅ ማሳያ መሆኑንም ተናግረዋል። ከእነዚህ ሁሉ ባሻገር በኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በመሠረተ ልማት ዘርፎች እየተመዘገቡ ያሉ ውጤቶች የአፍሪካ ሀገራትን ያስተሳሰሩና ኢኮኖሚያዊ የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋገጡ ናቸው ብለዋል። በተለይም ግዙፉ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ፣ ዘመናዊ የባቡርና የመንገድ መሠረተ ልማቶች በቀጣናው ሀገራት እየፈጠሩ የሚገኙትን ውህደትና የጋራ ተጠቃሚነትን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያ ለህብረቱ አጀንዳዎች መሳካት በምሳሌነት እያከናወነቻቸው ያለችው ተግባራትን ይበልጥ ለማሳደግ እየተተገበሩ የሚገኙ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ምቹ መደላድል የሚፈጥሩ መሆናቸውን አመላክተዋል።
በወለጋ ዞኖች እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ፕሮጀክቶች ለአካባቢው ማህበረሰብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ትልቅ እድል ይፈጥራሉ
Feb 26, 2026 85
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ወለጋ ዞኖች እየተከናወኑ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች ለአካባቢው ማህበረሰብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ትልቅ እድል ይዘው የመጡ መሆናቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል። ሰሞኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በምዕራብ፣ በቄለምና በምስራቅ ወለጋ ዞኖች የተለያዩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን የጎበኙ ሲሆን ከፊሎቹንም አስመርቀው ስራ ማስጀመራቸው ይታወሳል። በኦሮሚያ ክልል በተያዘው በጀት ዓመት ስድስት ወራት ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት 33 ቢሊዮን ብር ገቢ ተገኝቷል ከፕሮጀክቶቹ የመስኖ ግድብ፣ የከሰል ድንጋይ ማምረቻ ፋብሪካ፣ የወርቅ ማምረቻ፣ የበቆሎ ዱቄት መፍጫ ፋብሪካ፣ ኮሪደር ልማቶችና ሌሎች የልማት ስራዎች ይጠቀሳሉ። ነዋሪዎቹ ወደ ስራ የገቡ ፕሮጀክቶች የዓመታት የልማት ጥያቄዎቻቸውን በአግባቡ የሚመልሱ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል የሌቃ ዋዩ አባ ገዳ ተስፋ ዲልጋሳ እንደተናገሩት፣ የተመረቁ ፕሮጀክቶች የአካባቢውን ህዝብ የልማት ጥያቄ ከመመለስ ባለፈ ተጠቃሚነትን የሚያሳድጉ ናቸው። በልማት ፕሮጀክቶቹ ግንባታ ሂደትም በርካታ የአካባቢው ወጣቶች የስራ እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው የልማት ስራው ትልቅ ተስፋ እና መነቃቃትን የፈጠሩ መሆናቸውንም ተናግረዋል። በተጨማሪም እየተከናወን የሚገኘው የኮሪደር ልማት ከተሞችን በማስዋብ ለኑሮ ምቹና ተስማሚ በማድረግ የንግድ እንቅስቃሴን እያነቃቃ መሆኑን አንስተዋል። በምስራቅ ወላጋ ዞን ጊዳ ወረዳ ነዋሪዋ ወይዘሮ ማርታ አብዲሳ በበኩላቸው፤ ፕሮጀክቶቹ ከዚህ በፊት ስንጠይቅ የነበረውን የልማት ጥያቄዎች የሚመልሱ በመሆናቸው ተደስተናል ብለዋል።   የልማት ስራዎቹ ለአገልግሎት መብቃት ለአካባቢው ወጣቶች ትልቅ ተስፋ የሚሰጡ መሆናቸውንም አክለዋል። የምዕራብ ወለጋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ተሊላ ተረፋ እንደተናገሩት፤ ከዚህ በፊት የተጓተቱ የነበሩ የልማት ፕሮጀክቶች መንግስትና ህዝብ ተቀናጅተው በመስራታቸው ለውጤት መብቃታቸውን አስረድተዋል።   ፕሮጀክቶቹ ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የስራ እድል ከመፍጠርም ባለፈ የመብራት፣ ውሃ፣ የመንገድ ልማትና የጤና ተቋማት ማስፋፈያ ስራዎች ለህብረተሰቡ ትልቅ ጥቅም የሚሰጡ ናቸው ብለዋል።
በጉራጌ ዞን በበጋ መስኖ ወደ 27 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቷል
Feb 26, 2026 47
ወልቂጤ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፡- በጉራጌ ዞን በበጋ መስኖ ወደ 27 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መልማቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በእንስሳት እና ዓሣ ሀብት ልማት ከፍተኛ ለውጥ እየተመዘገበ ነው-ግብርና ሚኒስቴር የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ እና ግብርና መምሪያ ኃላፊ አበራ ወንድሙ እንዳሉት፣ በተያዘው በጋ ወቅት 26ሺህ 781 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በመስኖ መልማቱንና ከ6 ነጥብ 4 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ገልጸዋል። በእስካሁኑ ሂደትም 3 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል ምርት መሰብሰቡን አስረድተዋል።   በዞኑ የተለያዩ የሰብል እና የአትክልት ዓይነቶች በጥራትና በብዛት እየተመረቱ መሆኑን ገልፀው በአካባቢው ከዚህ ቀደም ተመርተው የማያውቁ እንደ ጥቁር አዝሙድ እና ኮረሪማ ያሉ የቅመማቅመም ዓይነቶች እየተመረቱ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዞኑ አበሽጌ ወረዳ የፈንጣ ቀበሌ አርሶ አደር ሙሃጅር በድሩ ከአራት ዓመታት ወዲህ እየተሳተፉባሉበት ያለው የበጋ መስኖ ልማት ኑሯቸውን በመለወጥ ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን ማሳደጉን ገልፀዋል።   ዘንድሮም የተመቻቸላቸውን እድል በመጠቀም በሁለት ሄክታር መሬት ላይ የዘር ሽንኩርት በመስኖ እያለሙ መሆናቸውንና የተሻለ ምርት ለማግኘት እየሰሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ከዝናብ ጥገኝነት ወጥተው በዓመት ከሁለት ጊዜ በላይ በመስኖ በማልማት ተጠቃሚ በመሆናቸው ወደ ዘርፉ መግባታቸውን የተናገሩት ደግሞ በቸሃ ወረዳ የአዘርናሲሰ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር ዘመቻ አሰና ናቸው።   መንግስት ባመቻቸላቸው የእርሻ መሬት፣ ምርጥ ዘር፣ ማዳበሪያ እና የሙያ ድጋፍ በመታገዝ ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን የተሻለ ደረጃ ላይ ማድረስ መቻላቸውን ገልጸዋል። መስኖ በስፋት እና በውጤታማነት ማምረት እንደሚቻል ለአካባቢው ህብረተሰብ ግንዛቤን በመፍጠር ረገድ የበኩላቸውን እየተወጡ መሆኑን ገልጸው በአካባቢው ታርሶ የማያውቅ መሬትን ወደ ምርታማነት ቀይረናል ብለዋል።
በዞኑ ሴቶች በሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር  ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ ነው
Feb 26, 2026 63
አምቦ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሸዋ ዞን በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የተሳተፉ ሴቶች በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ፍጆታቸውን ከመሸፈን ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መሆናቸውን ገለጹ። ከመርሐ ግብሩ ተጠቃሚዎች መካከል በኤጀሬ ወረዳ በዶሮ እርባታ ሥራ የተሰማሩት ወይዘሮ መስቱ ካሳሁን ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ 10 ሴቶች ሆነው በማህበር ተደራጅተው ወደ ሥራ መግባታቸውን ገልጸዋል። የልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም ዜጎችን ከተረጂነት ወደ አምራችነት እያሸጋገረ ነው በመጀመሪያ 1 ሺህ 300 የሥጋና የእንቁላል ጣይ ዶሮዎችን በማርባት የጀመሩ ሲሆን፣ አሁን ላይ የዶሮዎቹን ብዛት ወደ 3 ሺህ 800 በማድረስ ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል።   ወይዘሮ መስቱ አክለውም በአሁኑ ወቅት በቀን 700 እንቁላሎችን እያገኙ መሆኑን የገለጹ ሲሆን ምርታቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ ለአካባቢው ገበያ እያቀረቡም ነው። ከሽያጩ በሚያገኙት ገቢ ቤተሰባቸውን በጥሩ ሁኔታ እያስተዳደሩና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውንም እያሳደጉ መሆኑን ገልጸዋል። በተመሳሳይ በወተት ላሞች እርባታ የተሰማሩት ወይዘሮ ባይሴ ቱሉ፣ ቀደም ሲል በቀን ሥራ ይተዳደሩ እንደነበር አስታውሰዋል።   የሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር ከተጀመረ ወዲህ ግን፣ በቀን ከአንድ ላም በአማካይ 10 ሊትር ወተት ለገበያ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል። የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ዕለታዊ ገቢያቸውን ማሳደግ መቻላቸውን ገልጸው ለዚህ ስኬት የወረዳው ሴቶች እና ህጻናት ጉዳይ ጽሕፈት ቤት እና የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ጽሕፈት ቤት የሰጧቸው ሥልጠና ትልቅ እገዛ ማድረጉን ጠቅሰዋል። የኤጀሬ ወረዳ ሴቶች እና ህጻናት ጉዳይ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ሃና ኃይለማርያም ፤ በበጀት ዓመቱ ለ1 ሺህ 15 ሴቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ እንደነበረ ገልጸዋል።   በተከናወኑ የተቀናጁ ሥራዎች 1 ሺህ 600 ሴቶችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰው ሴቶቹ በከብት ማድለብ፣ በዶሮ እርባታ፣ በወተት ላም እርባታና በሌሎችም የሥራ ዘርፎች መሰማራታቸውን አስረድተዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን የሴቶችና ሕፃናት ጉዳይ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ክብቱ ድሪባ በበኩላቸው፣ በዞኑ የሴቶችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የግብርናና ሌሎች ኢኒሼቲቮች ውጤት እያመጡ መሆኑን ገልጸዋል።   እንደ ኃላፊዋ ማብራሪያ፣ በበጀት ዓመቱ ለ20 ሺህ ሴቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ፣ እስካሁን ለ19 ሺህ 250 ሴቶች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል። ሴቶች የቤተሰባቸውን የምግብ ፍጆታ ከመሸፈን ባለፈ ምርታቸውን ለገበያ በማቅረብ ለሌሎች አርሶ አደሮች አርአያ እየሆኑ መሆኑንም ገልጸዋል።
በመስኖ ካለማነው በርበሬና የጓሮ አትክልት ልማት ተጠቃሚ ሆነናል - አርሶ አደሮች
Feb 26, 2026 70
ሳውላ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በጎፋ ዞን በመደበኛ መስኖ በርበሬና ሌሎች የጓሮ አትክልቶችን በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ ከ9 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሽንኩርት፣ በቃሪያ፣ በበርበሬና በሌሎች የጓሮ አትክልቶች መሸፈኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታውቋል። የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ስራ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያሳደገው ነው አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በበጋ መስኖ የተለያዩ የጓሮ አትክልቶችን በማልማት ከሽያጩ ከ800 ሺህ እስከ 2 ሚሊዮን ብር ገቢ ማግኘት ችለዋል። ወጣት አርሶ አደር ታሪኩ እርሳሴ፤ በዞኑ ኡባ ደብረ ፀሀይ ወረዳ የሸሌ ቡኔ ቀበሌ ነዋሪ ሲሆን ላለፉት ስድስት ዓመታት በበጋ መስኖ ስራ ላይ መሰማራቱን ነው የገለፀው።   አርሶ አደሩ ባለው ሁለት ሄክታር ማሳ ላይ በርበሬ፣ ቲማቲም፣ ሽንኩርትና ሌሎች የጓሮ አትክልቶችን እያለማ ሲሆን በገበያ ላይ ያለውን ተፈላጊነት መሰረት አድርጎ የበርበሬና የሚጥሚጣ ምርት ላይ ማተኮሩን ይገልፃል። ከሚጥሚጣ ምርት ብቻም 2 ሚሊዮን ብር ገቢ እያገኘ መሆኑን የገለፀው አርሶ አደር ታሪኩ ከራሱ አልፎ ለ30 ሰዎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ ዕድል መፍጠሩንም ጠቁሟል።   ወጣት አሰበ አበራ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋም በዲግሪ ተመርቆ ሲቪውን ይዞ ስራ ከማፈላለግ ይልቅ ያለውን ፀጋ በመመልከት ከአባቱ ጋር በመሆን ሽንኩርትና በርበሬ ልማት ላይ በመሰማራት የተሻለ ተጠቃሚ መሆን መቻሉን ይናገራል።   ወጣቱ አርሶ አደር በሩብ ሄክታር ማሳ ላይ ካለማው ሽንኩርትም 40 ሺህ ብር የተጣራ ገቢ እንዳገኘ ነው የሚገልፀው። የኡባ ደብረ ጸሀይ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አገኘሁ ሲራጅ በበኩላቸው፤ በወረዳው ከ1 ሺህ 20 ሄክታር በላይ መሬት በጓሮ አትክልት እየለማ እንደሆነ ተናግረዋል።   በዋናነት ሽንኩርት፣ በርበሬ፣ ጥቅል ጎመንና ሀባብ በማምረት አርሶ አደሩ ተጠቃሚ እየሆነ መምጣቱንም አመልክተዋል። በዞኑ በበጋ መስኖ ከ9 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የጓሮ አትክልቶች የተሸፈነ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጎፋ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ዳንኤል ደግፌ ናቸው።   በዋናነት በበርበሬና ሚጥሚጣ ልማት ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች በከፍተኛ ደረጃ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ነው የገለጹት። እንደ ኃላፊው ገለፃ አንድ አርሶ አደር በስድስት ሄክታር ካለማው ሚጥሚጣ እስከ ሁለት ሚሊዮን ብር ገቢ ማግኘት እንደቻለም ነው የተናገሩት።
በእንስሳት እና ዓሣ ሀብት ልማት ከፍተኛ ለውጥ እየተመዘገበ ነው-ግብርና ሚኒስቴር
Feb 25, 2026 207
አዲስ አበባ ፤የካቲት 18 /2018 (ኢዜአ)፡-ባለፉት ጥቂት ዓመታት አዳዲስ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን ተግባራዊ በማድረግ በእንስሳት እና ዓሣ ሀብት ልማት ከፍተኛ ለውጥ መመዝገቡን ግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። ግብርና ሚኒስቴር ቅንጅታዊና ተቋማዊ አሰራርን ለማጠናከር፣ ሀገር አቀፍ የእንስሳት እና ዓሣ ሀብት ኤክስቴንሽን ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ አካሂዷል።   በዚሁ ወቅት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት አዳዲስ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን ተግባራዊ በማድረግ በሀገሪቱ የእንስሳት እና ዓሣ ሀብት ልማት ላይ ከፍተኛ ለውጥ ተመዝግቧል። ቀደም ሲል በስትራቴጂ ደረጃ ተዘንግቶ የቆየው ይህ ዘርፍ፣ አሁን ራሱን ችሎ እንዲደራጅና ልዩ የመንግስት ትኩረት እንዲሰጠው በመደረጉ አመርቂ ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑ ገልጸዋል። የእንስሳት እና ዓሣ ኤክስቴንሽን መተግበር ከጀመረ ወዲህ ለአርሶና አርብቶ አደሩ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችና እውቀቶችን ተደራሽ ማድረግ መቻሉን ጠቁመዋል። በዚህም በእንስሳት ጤና አጠባበቅና በምርታማነት ላይ ተጨባጭ ለውጥ መጥቷል ብለዋል። የእንስሳት በሽታ የዘርፉ ዋነኛ ተግዳሮት ሆኖ መቆየቱን ጠቁመው በአሁኑ ወቅት አርሶ አደሮች በባለሙያ የታገዘ በሽታን መከላከያ ዘዴዎችን በመጠቀማቸው ውጤታማ እየሆኑ መጥተዋል ብለዋል። ምንም እንኳን እስካሁን የተከናወኑ ስራዎች ተስፋ ሰጭ ቢሆኑም፣ አሁንም በዝርያ ማሻሻያና በዘመናዊ የእንስሳት ጤና አጠባበቅ ረገድ ያሉ ክፍተቶችን ለመሙላት የሁሉም አካላት ተሳትፎ መጠናከር እንዳለበት ገልጸዋል። መንግስት ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ በነደፋቸው የተለያዩ ኢኒሼቲቮች አማካይነት፣ ኢትዮጵያ ካላት እምቅ የእንስሳት ሀብት የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ በትኩረት እንደሚሰራ ጠቁመዋል። የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አሰፋ ፎና በበኩላቸው በእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት በክልሉ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት የእንስሳትን ዝርያ ማሻሻል ላይ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የእንስሳት እና ዓሣ ሀብት ዘርፍ ኃላፊ ታመነ በቀለ በበኩላቸው የእንስሳት ምርትና ምርታማነት ለማሻሻል ዘመናዊ የእንስሳት መኖ ልማት መጀመሩን ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ እንስሳት ሐኪሞች ማህበር ዋና ስራ አስፈጻሚ ፕሮፌሰር እንድሪያስ ዘውዱ የእንስሳት ጤና ኤክስቴንሽን ለዘርፉ ዕድገት ትልቅ ሚና እንዳለው ገልጸው፥ ማህበሩ በእንስሳት ጤና ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።  
የኢትዮጵያ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስኬቶች የከተሞችን ትንሳኤ በማብሰር ዘመናዊ የአኗኗር ምዕራፍ የከፈቱ ናቸው
Feb 25, 2026 161
አዲስ አበባ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስኬቶች የከተሞችን ትንሳኤ በማብሰር ዘመናዊ የአኗኗር ምዕራፍ የከፈቱ መሆናቸውን የምህንድስና ባለሙያዎች ገለጹ። በአዲስ አበባ የተጀመረው የኮሪደርና ከተማ ዕድሳት የልማት ሥራ አሁን ላይ ተደራሽነቱን በማስፋት በርካታ ከተሞችን ውብ ገጽታ ማላበስ ያስቻለ እመርታዊ ስኬት እያስገኘ ነው። የከተሞች የኮሪደርና ዕድሳት የልማት ሥራም ዘመናዊ ኢኮኖሚ፣ አስተዳደር፣ ከባቢ፣ እንቅስቃሴ፣ ነዋሪና የአኗኗር ሥርዓትን የሚያጎናጽፉ ስትራቴጂክ አቅጣጫዎችን የተከተሉ ናቸው። ለአብነትም በ2018 ዓ.ም የበጀት ዓመት ሃያ አንድ የኢትዮጵያ ከተሞችን ለነዋሪዎችና ጎብኝዎቻቸው ምቹ ገጽታን ማላበስ የሚያስችል ዘመናዊ የመሰረተ ልማት ግንባታ እየተከናወነ ይገኛል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ የምህንድስና ሙያተኞችም፤ የኢትዮጵያ ከተሞች የኮሪደርና የዕድሳት የልማት ሥራ ታሪክን ከዘመናዊነት በማሰናሰል ምቹ የአኗኗር ዘይቤን ማጎናጸፍ የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርስቲ የስማርት ሲቲ ባለሙያ ዮዲት ገብረአሊፍ (ዶ/ር)፤ የኮሪደር ልማት ከመሠረተ ልማት ግንባታ ባሻገር ዜጎችን ስልጣኔና ዘመናዊ አኗኗር የሚያጎናጽፍ ነው ብለዋል። ለአብነትም አዲስ አበባን ውብ ገጽታ ያላበሷት የኮርደርና የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎቶች ለዘመናዊ ከተማ ግንባታ ትርጉም የሚሰጣቸው ወሳኝ የልማት መሠረቶች መሆናቸውን ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የሥነ-ህንፃ መምህርና የከተማ ፕላን ባለሙያ መስፍን አለሙ፤ የኮሪደር ልማቱ ከተሞች በዘፈቀደ የሚመሩበትን ተለምዷዊ አሰራር በመቀየር ማራኪና ውብ ገጽታ ማላበስ ያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በኢትዮጵያ ከተሞች የኮርደር ልማት የተመዘገቡ አስደናቂ ለውጦች የከተሞችን ትንሳኤ በማብሰር ዘመናዊ የአኗኗር ዘይቤን በመፍጠር አዲስ ምዕራፍ የከፈቱ ናቸው ብለዋል።   የኮሪደርና ከተማ ዕድሳቱም ነዋሪዎችና ጎብኝዎች ጤናማ የእንቅስቃሴ ሥርዓት እንዲጎናጸፉ በማስቻል ለከተሜነት ግንባታ ትርጉም የሚሰጣቸው መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊ የከተማ ልማት ተግባራትም ዜጎችን ከሚያጎናጽፋቸው ዘመናዊ አኗኗር ሥርዓት ባሻገር የተቋማትን አገልግሎቶች በማዘመን የአገልግሎት እርካታን መፍጠር እንደሚያስችሉ ሙያተኞቹ አንስተዋል። ኢትዮጵያዊያንም የከተሞችን ማራኪ የልማት ሥራዎች በባለቤትነት በመጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላለፉ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው አንስተዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያ ከተሞችን ዘመናዊ ገጽታ የማላበስ ተግባር በማስቀጠል በዕውቀትና ክህሎት የሚመሩና ጤናማ ዕድገትና አገልግሎት የሚከተሉ ከተሞችን መገንባት እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።
በአማራ ክልል በምርጥ ዘር ከለማው መሬት እስካሁን 131 ሺህ ኩንታል በላይ ዘር ተሰብስቧል
Feb 25, 2026 104
ባህርዳር፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦ በ2017/2018 የምርት ዘመን በምርጥ ዘር ከተባዛው መሬት ከ131 ሺህ ኩንታል በላይ ዘር መሰብሰቡን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቅድመ-በልግ በዘር ከተሸፈነው የበቆሎ ማሳ የተሻለ ምርት እንጠብቃለን የቢሮው የዘር ብዜት ባለሙያ አቶ ጥላዬ ሞገሴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የዘር ብዜት ላይ በተለየ ትኩረት እየተሰራ ይገኛል። በምርት ዘመኑ በዘር ብዜት ከተሸፈነው ከ10 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት 232 ሺህ 589 ኩንታል ዘር ለመሰብሰብ ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   እስካሁን በተደረገው ጥረትም 131 ሺህ 676 ኩንታል የበቆሎ፣ የስንዴ፣ የሩዝ፣ የጤፍ፣ የማሽላ፣ የሰሊጥ፣ የቅባትና የጥራጥሬ እህል ዘር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። በአማራ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ፣ በዩኒየኖች፣ በግል ዘር አባዢዎችና ድርጅቶች የሚካሄደውን የዘር ብዜት እስከ መጋቢት ወር አጋማሽ ሰብስቦ በማጠናቀቅ ለአርሶ አደሩ ለማድረስ ዝግጅት እንደሚደረግ ነው የገለጹት። እስካሁን በተደረገ የተቀናጀ ጥረትም የበቆሎ ዘር ፍላጎት ማሟላት መቻሉን ጠቁመው ሌሎች የሰብል ዘሮችን በሚፈለገው ልክ በማባዛት ለማቅረብ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል።   በምዕራብ ጎጃም ዞን ቡሬ ዙሪያ ወረዳ በዘር ብዜት ተግባር የተሰማሩት አቶ ቢኒያም ሙላት፤ በ48 ሄክታር መሬት ላይ ያባዙትን የበቆሎ ዘር ሰብስበው ወደ መጋዘን እያጓጓዙ መሆኑን ተናግረዋል። የምርት ዘመኑ ለዘር ብዜት ስራው አመቺ ሆኖ በመገኝቱ የተሻለ ምርት ለመሰብሰብ አስችሎኛል ብለዋል። በ62 ሄክታር መሬት ያባዙትን ቢኤች 561 የበቆሎ ዘር ጥራቱን በጠበቀ አግባብ ሰብስበው እያጠናቀቁ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የወንበርማ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አቶ ሰማኸኝ ሽዋፈራው ናቸው። ዘሩን በቀጣይ አበጥረውና በተለያየ መጠን አሽገው ለአርሶ አደሩ በወቅቱ ለማቅረብ እየተዘጋጁ እንደሚገኙም ተናግረዋል። በክልሉ በ2016/2017 የምርት ዘመን በዘር ከተሸፈነው 14 ሺህ ሄክታር መሬት 281 ሺህ ኩንታል ዘር በመሰብሰብ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የማር ልማት ኢኒሼቲቭ ተግባራዊ መደረጉ ተጨማሪ ገቢ እንድናገኝ አስችሎናል - አርሶ አደሮች
Feb 25, 2026 112
ሮቤ ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦የማር ልማት ኢኒሼቲቭ ተግባራዊ መደረጉ ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ተጠቃሚ አድርጎናል ሲሉ በባሌ ዞን የሐረና ቡሉቅና ደሎ መና ወረዳ አርሶና አርብቶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ ባለፉት ስድስት ወራት ለማር ልማት ኢኒሼቲቭ በተሰጠው ትኩረት ከ8 ሺህ ቶን በላይ የማር ምርት መገኘቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገልጿል። በኦሮሚያ ክልል እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ከሚገኝባቸው አካባቢዎች አንዱ በሆነው ባሌ ዞን ማር በስፋት ይመረታል። የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ አድርጎናል ይሕንኑ መነሻ በማድረግም ጥራቱን የጠበቀ የማር ምርት ለገበያ ለማቅረብ በተከናወኑት ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እየታየ መጥቷል። በዞኑ ሐረና ቡሉቅና ደሎ መና ወረዳ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንዳሉት፤ በአካባቢው ተግባራዊ የተደረገው የማር ልማት ኢኒሼቲቭ ምርታማነትን ያሳደገ በመሆኑ ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት አስችሎናል ብለዋል። አርሶ አደር ሁሴን አህመድ እንዳሉት፤ ባለፉት ሁለት ዓመታት ዘመናዊ የንብ ቀፎዎችን በመጠቀምና የተሻሻሉ አሰራሮችን በመተግበር ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ መቻላቸውን ገልጸዋል።   በዚህም ከአንድ ባህላዊ ቀፎ ይገኝ የነበረውን 7 ኪሎ ግራም ማር ወደ 20 ኪሎ ግራም ለማሳደግ ከመቻሉ ባለፈ ተጨማሪ ገቢ በማግኘት የተሻለ ኑሮ ለመምራት አስችሎኛል ነው ያሉት። መንግስት በተመጣጣኝ ዋጋ በሚያቀርበው ዘመናዊ ቀፎ መጠቀም በመቻላቸው የማር ምርታቸውን ለማሳደግ እንደቻሉ የሚገልጹት ደግሞ በደሎ መና ወረዳ በንብ ማነብ ስራ ላይ የተሰማሩት አቶ አብዶ ከድር ናቸው።   ባለፉት ዓመታት በአካባቢያቸው የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ስራዎች ለንብ ማነብ ስራ እድገትና መስፋፋት አመቺ ሁኔታዎችን እንደፈጠረላቸውም ነው ያመለከቱት። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ጌታቸው አበባ በበኩላቸው፤ የማር ምርት ኢኒሼቲቭ በዞኑ ያለውን እምቅ አቅም በመጠቀም የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማሳደግ እያስቻለ መጥቷል ብለዋል።   ኢኒሼቲቩ ከመጀመሩ በፊት የዞኑ ዓመታዊ የማር ምርት ከ2 ሺህ ቶን የማይበልጥ ነበር ያሉት ኃላፊው ኢኒሼቲቩ ተግባራዊ በመደረጉ ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ ከ8 ሺህ ቶን በላይ ማር ማምረት እንደተቻለ ተናግረዋል። በዞኑ የነበረውን ከ20 ሺህ የማይበልጥ የዘመናዊ ቀፎ ብዛት በአሁኑ ወቅት ከ85 ሺህ በላይ ማድረስ መቻሉንም አንስተዋል። በመስኩ እየታየ ያለው ውጤትም ዘመናዊ የንብ ቀፎዎችን ለአርሶ አደሩ በስፋት ከማቅረብ ባሻገር በዘርፉ የተሻለ ግንዛቤ ለመፍጠር በመቻሉ እንደሆነም አስረድተዋል። ኢኒሼቲቩ የዘርፉን ምርታማነት ከማሳደግ ባሻገር 2 ሺህ ለሚበልጡ ወጣቶች የሥራ ዕድል የፈጠረ መሆኑንም አመልክተዋል።
አዳዲስ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በመተግበር በእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት እመርታ ተመዝግቧል
Feb 25, 2026 145
አዲስ አበባ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦ አዳዲስ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን ተግባራዊ በማድረግ በሀገሪቱ የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ላይ ከፍተኛ እመርታ መመዝገቡን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። የተገኘውን ውጤት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገርም የባለድርሻ አካላት ቅንጅት ወሳኝ መሆኑ ተጠቁሟል። የግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥሯል ግብርና ሚኒስቴር ሀገር አቀፍ የእንስሳት እና ዓሣ ሃብት ኤክስቴንሽን የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ እያካሄደ ነው፡፡   በዚሁ ወቅት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የእንስሳት ልማት ትልቅ እመርታ አሳይቷል። አዳዲስ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን በመተግበር በእንስሳት እና ዓሣ ሀብት ላይ አመርቂ ውጤቶች ተመዝግበዋል ነው ያሉት። የእንስሳት ሀብት ልማት ቀደም ሲል በስትራቴጂ ደረጃ ተዘንግቶ የቆየ ቢሆንም፣ አሁን ግን ራሱን ችሎ እንዲደራጅና ትኩረት እንዲሰጠው መደረጉን አንስተዋል። የኤክስቴንሽን ሥርዓትን በመተግበር በእንስሳት ጤናና ምርታማነት ላይ እውቀትንና ቴክኖሎጂን ለአርሶ አደሩ በማስተዋወቅና እንዲጠቀም በማድረግ ለውጥ መምጣቱንም ገልፀዋል። አርሶ እና አርብቶ አደሮች በባለሙያ የታገዘ የእንስሳት በሽታን በመከላከል ረገድ ውጤታማ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። በምርምር የተገኙ ቴክኖሎጂዎችን፣ የዝርያ ማሻሻያ ሥራዎችንና የእንስሳት ጤና አጠባበቅ ዘዴዎችን ተግባር ላይ ለማዋል ሰፊ ክፍተት ቢኖርም፣ የተጀመሩት ሥራዎች ተስፋ ሰጭ እንደሆኑ አስረድተዋል። የተገኙ ውጤቶችን ይበልጥ ለማጠናከር የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም