ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በክልሉ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜና ጥራት እየተጠናቀቁ ናቸው
Jun 29, 2026 736
ነቀምቴ ፤ሰኔ 22/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የህብረተሰቡን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማቀላጠፍና የልማት ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜና ጥራት እየተጠናቀቁ መሆኑ ተገለጸ። በምስራቅ ወለጋ ዞን ዋዩ ቱቃ ወረዳ በ99 ሚሊየን ብር በላይ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። በፕሮጀክት ምረቃ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል ገቢዎች ቢሮ ምክትል ሀላፊ አቶ ለሜሳ አየለ እንደገለፁት፤ መንግስት የአገልግሎት አሰጣጥን ለማቀላጠፍና የህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ ነው። በዚህም ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው የጊዜና የጥራት ደረጃ እንዲጠናቀቁ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። ዛሬ ለአገልግሎት ክፍት የተደረጉት ፕሮጀክቶችም የስራ እድል የሚፈጥሩና የዞኑን የገቢ አቅም የሚያሳድጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። የምስራቅ ወለጋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ደሱ ለሚ በበኩላቸው፤ መንግስት የአገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን የህብረተሰቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ለመፍታት መስራቱን አንስተዋል። ከህብረተሰቡ ጋር በመቀናጀት ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ወደ ስራ ማስገባቱን ተናግረዋል። ለአገልግሎት ክፍት ከተደረጉት ፕሮጀክቶች መካከል የስራ እድልን ማስፋት የሚያስችሉ የመስሪያና የመሸጫ ቦታዎች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል። በብልፅግና ፓርቲ የምስራቅ ወለጋ ዞን ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ፍቃዱ ገመዳ በበኩላቸው፤ መንግስት ለህብረተሰቡ የልማት ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የገባውን ቃል ለመፈጸም በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም እየተከናወኑ ባሉ ስራዎች ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑን ጠቁመው ለዚህም የዛሬዎቹ ፕሮጀክቶች ማሳያ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የዋዩ ቱቃ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አማኑኤል መኮንን በበኩላቸው ፤ከ99 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ የከብት እርባታ ማእከል ፣ ድልድዮች ፣ መንገዶች ፣ የቡሳ ጎኖፋ እህል ማከማቻ መጋዘን እና ሌሎች ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን ገልጸዋል። የልማት ፕሮጀክቶቹም ለማህበረሰቡ ጥያቄ ምላሽ የሚሰጡና የወረዳውን ማህበረሰብ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እንደሚያሳልጡ ጠቁመዋል።
ቢሮው ተግባራዊ ያደረጋቸው በቴክኖሎጂ የተደገፉ አዳዲስ አሠራሮች የከተማዋን የገቢ አቅም አሳድጓል
Jun 29, 2026 521
አዲስ አበባ፤ሰኔ 22/2018(ኢዜአ)፦ተግባራዊ ያደረጋቸው በቴክኖሎጂ የተደገፉ አዳዲስ አሠራሮች የአገልግሎት አሰጣጡን ከማዘመን ባለፈ የከተማዋን የገቢ አቅም ማሳደጉን የአዲስ አበባ ከተማ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ፡፡ ቢሮው ቀደም ሲል ግብር ከፋዮች በአካል በመቅረብና የወረቀት ሰነዶችን በመያዝ ያገኙት የነበረውን አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ ወደ ኦንላይን ሥርዓት ማሸጋገር ችሏል። የአዲስ አበባ ከተማ ገቢዎች ቢሮ የሞደርናይዜሽን ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ መሃመድ አብዱረህማን ለኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ ቢሮው ባለፉት ሁለት ዓመታት በርካታ የሪፎርም ሥራዎችን አከናውኗል። ግብር ከፋዮች በአካል ሳይመጡ በኢሜል እና በተዘረጋው የኦንላይን ሊንክ አገልግሎቱን ማግኘት እንዲችሉ ከፌደራል ገቢዎች ሚኒስቴር ጋር በመቀናጀት የተቀናጀ የልማት ሥርዓት ተዘርግቶ ወደ ተግባር መገባቱን ጠቁመዋል። ይህ አዲስ አሠራር ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው አገልግሎት የሚያገኙበትን ምኅዳር የፈጠረ ሲሆን፣ የባለቤትነት ስም ዝውውርን ጨምሮ የተለያዩ የሕግ ተገዥነት አገልግሎቶችን ያካተተ መሆኑን አስረድተዋል። ቢሮው በራሱ አቅም ያለማውን የዕዳ ክትትል ሥርዓት ወደ ተግባር በማስገባቱ በ17ቱም ቅርንጫፎች የሚወሰኑ የዕዳ ውሳኔዎችን በቅርበት ለመከታተልና የሚሰበሰበውን ገቢ ወደ ገንዘብ በመለወጥ ረገድ ከፍተኛ አፈጻጸም ተመዝግቧል። የክሊራንስ አሰጣጥ ሂደቱን ይበልጥ ግልጽ፣ ቀልጣፋና እምነት የሚጣልበት ለማድረግ ባርኮድ ያለው አዲስ የኦንላይን አሠራር ተግባራዊ መደረጉንም ተናግረዋል፡፡ የተዘረጉት የዲጂታል አገልግሎቶች ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው ግብራቸውን እንዲያሳውቁና እንዲከፍሉ በማድረጉ፣ በየወሩ መጨረሻ ላይ በቅርንጫፍ ቢሮዎች ይታይ የነበረውን ከፍተኛ መጨናነቅና የረጅም ጊዜ ጥበቃ ማስቀረት መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡ ቢሮው በቀጣዩ በጀት ዓመትም የደረጃ "ለ" ግብር ከፋዮችን የሚያስተናግደውን የኢቲ ታክስ (eTax) ሥርዓት ሙሉ ለሙሉ ወደ ዲጂታል በማሸጋገር፣ ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችሉ ማሻሻያዎችን እንደሚተገብር ገልጸዋል። በከፍተኛ ግብር ከፋዮች ቅርንጫፍ የኤሌክትሮኒክስ ታክስ ግብይት ድጋፍና ክትትል የሥራ ሂደት ተወካይ አቶ ሰይድ መሃመድ፤ ለግብር ከፋዮች ስለ አገልግሎቱ አጠቃቀም በቂ ስልጠናና ተከታታይ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የቅርንጫፉ የኤሌክትሮኒክስ ታክስ ክፍያ አሰባሰብና ክትትል ቡድን አስተባባሪ ተወካይ አቶ ኢድሪስ መሃመድ በበኩላቸው፣ አዲሱ የዲጂታል ሥርዓት ተቋማዊ አፈጻጸምን ከማሳደግና ሥራዎችን ከማቅለል አንጻር ሰፊ ፋይዳ እንዳለው አብራርተዋል። የቅርንጫፉ ተገልጋዮችም በአዲሱ አሠራር መደሰታቸውን ገልጸዋል፡፡ አዲሱ የኦንላይን ሥርዓት ረጅም ሰልፍን ያስቀረና ተገልጋዩ በቤቱ ሆኖ ሁሉንም አገልግሎት ማግኘት እንዲችል ያደረገ መሆኑን እና በዚህም ዘርፈ-ብዙ ጥቅሞችን እንዳስገኘላቸው ተናግረዋል፡፡ የዲጂታል አሠራሩ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ በማስቻል ይደርስባቸው የነበረውን ከፍተኛ እንግልት ሙሉ በሙሉ ማስቀረቱንም አረጋግጠዋል።
ዘላቂና አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ኃይልን በሁሉም አካባቢ ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ስትራቴጂ እየተዘጋጀ ነው
Jun 29, 2026 330
አዲስ አበባ፤ሰኔ 22/2018(ኢዜአ)፦ዘላቂና አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ኃይልን በሁሉም አካባቢ ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ስትራቴጂ እየተዘጋጀ መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የብሔራዊ የኤሌክትሪክ ተደራሽነት መርሃ ግብር ምዕራፍ ሦስት ትግበራን የተመለከተ አውደጥናት አካሂዷል። በዚህ ወቅት የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኢነርጂ ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ የኤሌክትሪክ ኃይል ለዕድገትና ለማንኛውም ዓይነት የልማት እንቅስቃሴ ወሳኝ ነው። በተመጣጣኝ ዋጋ የሚቀርብ ታዳሽ፣ ዘላቂና አስተማማኝ የኃይል ተደራሽነት የኢትዮጵያን ብልፅግና፣ ዕድገትና ዘላቂ ልማት ለማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑንም ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ያሏትን የኃይል አማራጭ ምንጮች ለመጠቀም የኃይል ማመንጨት አቅምን ማሳደግ፣ እንዲሁም የኃይል አማራጮችን የማሻሻል ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን ገልጸዋል። ለብሔራዊ የኤሌክትሪክ ተደራሽነት መርሃ ግብር ትግበራ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ እንዲያድግ ለማድረግ የኢነርጂ ፖሊሲ ክለሳ እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። በተጨማሪም መንግሥት ዘርፉን ለማጠናከር በርካታ ስትራቴጂዎችንና የሕግ ማዕቀፎችን ማዘጋጀቱን ጠቅሰዋል። የመጀመሪያውና ሁለተኛው የኤሌክትሪክ ተደራሽነት መርሃ ግብር ትግበራ ከዋናው መስመር ርቀው ባሉ አካባቢዎች የሶላር ቴክኖሎጂዎችን ለገጠሩ ማኅበረሰብ ተደራሽ በማድረግ ረገድ መሻሻል ያመጣ መሆኑን አብራርተዋል። በመርሃ ግብሩ የሦስተኛው ምዕራፍ ትግበራም ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ንጹሕ ኢነርጂን ማስፋፋት፣ ለምርታማነት ተግባራት ቅድሚያ መስጠትና የዘርፉን ዲጂታላይዜሽን አሠራር ማጠናከር ላይ የሚያተኩር መሆኑን ተናግረዋል። ለዚህ ምዕራፍ ትግበራ ከ18 ቢሊዮን ዶላር በላይ እንደሚያስፈልግ ጠቁመው በሁለቱ ምዕራፎች ያጋጠሙ ክፍተቶችን ለመፍታት በሚያስችል መልኩ የተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል። ቀጣናዊ የኃይል ትስስርን በማጠናከር ለሌሎች የአፍሪካ አገራት ኃይል በማቅረብ የአህጉሪቱን ሁለንተናዊና የተቀናጀ ልማት በማሳለጥ ቀጣናዊና አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደትን ለማጠናከር እየተሠራ መሆኑንም አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ፤ የኃይል ማመንጫ፣ ማስተላለፊያና ማከፋፈያ ጣቢያዎች ግንባታ ሥራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ትግበራ እስከ 2035 ድረስ ባሉት ዓመታት የኤሌክትሪክ ኃይልን በመላ አገሪቱ ለማዳረስ መታቀዱን የገለጹት ደግሞ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው ናቸው። በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኤሌክትሪፊኬሽንና ኢነርጂ መረጃ መሪ ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ዳቢ፤ የብሔራዊ የኤሌክትሪክ ተደራሽነትን የሚመራ ስትራቴጂ ለማዘጋጀት ከአንድ ዓመት በላይ ጥናት ሲካሄድ ቆይቷል ብለዋል። በስትራቴጂው የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት መንግሥት፣ ከልማት አጋሮችና ከግሉ ዘርፍ ጋር በትብብር እንደሚሠራም ገልጸዋል። የዓለም ባንክ የኢነርጂ ባለሙያ ወንድአየሁ ደምሴ በበኩላቸው፤ ባንኩ በኢነርጂ ዘርፍ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በትብብር እየሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። አሁንም በብሔራዊ የኤሌክትሪክ ተደራሽነት መርሃ ግብር የቴክኒክ ድጋፍ ማድረጉንና በቀጣይም ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል።
የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት የኢትዮጵያን የልማት ትልሞች በሚያረጋግጥ መልኩ የተዘጋጀ ነው
Jun 29, 2026 300
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 22/2018(ኢዜአ)፦ የ2019 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግሥት ረቂቅ በጀት የኢትዮጵያን የልማት ትልሞች በሚያረጋግጥ መንገድ መዘጋጀቱን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አስታወቀ። ቋሚ ኮሚቴው የመንግሥት ተቋማት የተመደበላቸውን በጀት በጥንቃቄና በአግባቡ ሥራ ላይ ማዋል እንዳለባቸውም አሳስቧል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በ2019 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግሥት ረቂቅ በጀት ላይ ከገንዘብ ሚኒስቴርና ከባለበጀት መሥሪያ ቤቶች ጋር የማጠቃለያ ውይይት አካሂዷል። በመድረኩ የረቂቅ በጀቱን ዝርዝር ማብራሪያ የሰጡት የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ፤ የ2019 በጀት ዓመት በጀት የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያን መነሻ አድርጎ መዘጋጀቱንና በአጠቃላይ ሀገራዊ የኢኮኖሚ ዕድገትን ይበልጥ የሚደግፍ መሆኑን ገልጸዋል። የ2019 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግሥት ረቂቅ በጀት ጠቅላላ መጠን 2 ትሪሊየን 339 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ሲሆን፥ ይህም ከ2018 በጀት ዓመት በጀት ጋር ሲነጻጸር የ 21 ነጥብ 3 በመቶ ጭማሪ አለው። የበጀት ድልድሉ ለመደበኛ በጀት 1 ትሪሊየን 236 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር ይህም እየተገባደደ ከሚገኘው በጀት ዓመት አንጻር የ16 ነጥብ 5 በመቶ ዕድገት አሳይቷል ብለዋል፡፡ በሌላ መልኩ ለካፒታል በጀት 568 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር እንዲሁም ለክልሎች የሚደረግ ድጋፍ 520 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የመድረኩ ተሳታፊዎች በየዓመቱ እያደገ የመጣው በጀት የሕዝቡን መሠረታዊ ጥያቄዎችና ፍላጎቶች እየፈታ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ ይሁን እንጂ በጀታቸውን በአግባቡ ባልተጠቀሙና ኃላፊነታቸውን ባልተወጡ አካላት ላይ ምን ዓይነት እርምጃዎች እየተወሰዱ እንደሚገኙ ጠይቀዋል። በተጨማሪም የመንግሥት ተቋማት የነዳጅ አጠቃቀም ከፍተኛ መሆኑን በመጥቀስ፥ ተቋማትን ከነዳጅ ጥገኝነት በማላቀቅ ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች (EV) ለማሸጋገር ምን ዓይነት ሥራዎች እየተሠሩ እንደሆነ ጥያቄ አቅርበዋል። ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ፤ በአሠራር ረገድ ክፍተት በተገኘባቸው አካላት ላይ ተጠያቂነትን የማስፈን ሥራ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት ከአስተዳደራዊ ቅጣት ጀምሮ አስተማሪ የሆኑ እርምጃዎች እየተወሰዱ እንደሚገኙ አመልክተዋል። አጠቃላይ በጀቱ ሀገራዊ ዕድገትንና የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋትን በሚያረጋግጥ መልኩ የተዘጋጀ በመሆኑ ተቋማት የተመደበላቸውን የሕዝብ ሀብት በጥንቃቄ ማስተዳደር እንዳለባቸው አሳስበዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጆ በበኩላቸው፤ የ2019 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግሥት ረቂቅ በጀት በጥሩ ሁኔታ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። በጀቱ የኢትዮጵያን የልማት ትልሞች የሚያሳካ መሆኑን ጠቁመው ተቋማት የተመደበላቸውን በጀት በጥንቃቄ ሥራ ላይ ማዋል እንዳለባቸው አሳስበዋል። ቋሚ ኮሚቴው በረቂቅ በጀቱ ላይ ያደረገውን ግምገማ በማጠናቀቅ በቀጣዩ ሳምንት ለምክር ቤቱ የውሳኔ ሐሳብ እንደሚያቀርብ ተገልጿል።
ቱሪዝም- የኢትዮጵያ የማከናወን አቅም ማሳያ
Jun 29, 2026 295
በዮሐንስ ደርበው “ሀገራችን ከቱሪዝም ልታገኛቸው የምትችላቸውን ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና አካባቢያዊ ጥቅሞች ሁሉ ከቀረው ዓለም ጋር ተወዳድራ እንድታገኝ፣ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ጎብኚ ወደ ሀገራችን መሳብ አለብን። ለዚህም የተለያዩ ስልታዊ መላዎች ነድፈን እየተንቀሳቀስን እንገኛለን (የመደመር መንግሥት 273)። የቱሪዝም ኢንዱስትሪ የለውጡ መንግሥት እመርታዎችን ካስመዘገበባቸው ዘርፎች አንዱ ነው። መንግሥት ከአምሥቱ የትኩረት መስኮች አንዱ አንድርጎም በጥናት፣ አካባቢያዊ ፀጋን ዐውቆና ለይቶ በተደመረ ዐቅም ባከናወናቸው ሥራዎች በገበታ ለሸገር፣ በገበታ ለሀገር፣ በገበታ ለትውልድ፣ በኮሪደር ልማት፣ በወንዝ እና የወንዝ ዳርቻዎች ልማት እሠየው ያሰኙ ተግባራት አከናውኗል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው ከእንጦጦ - ቀበና የተከናወነው የወንዝና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክትም ለጎብኚም ለነዋሪም ምቹ ከባቢን በመፍጠር ረገድ እየተደረገ ያለውን ትጋት ያስረዳል። ምረቃውን ተከትሎ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ባጋራው መረጃ፤ “መቆሸሽ እኛ አይገባንም፣ መጠልሸት እኛ አይገባንም፣ ማነስ እኛ አይገባንም! ሠርተን እንደምንችል ማሳየት ያስፈልጋል” ሲል የሥራውን ማራኪነትና ውበት ገልጿል። ጠቅላይ ሚኒስትሩም በዚሁ ወቅት፤ የተሰጠንን ሕዝባዊ አደራ በታማኝነት፣ በጽኑ ትጋት እና በቅንነት በመፈጸም የዜጎቻችንን የኑሮ ጥራት ለማሻሻልና መሠረታዊ ለውጥ ለማምጣት የጀመርነውን ጉዞ አበክረን እንቀጥላለን ሲሉ በቀጣይ ካለፈው የበለጠ እንደሚሠራ አመላክተዋል። ገንዘብን፣ ዕውቀትን፣ ጉልበትን፣ ሐሳብን፣ የአመራር ብቃትን ስንደምር የሚከሰተው ነገር እንደዚህ ያለው ውበት ይሆናል ሲሉም አስገንዝበዋል። በመደመር መንግሥት መጽሐፋቸው (ገጽ 256) ላይም፤ “የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ሀገራት በዘመናቸው ሁሉ የሠሩትንና ተፈጥሮ ያደለቻቸውን መልካም ገጽታ በኩራት ለዓለም የሚያስተዋውቁበት፣ ‘ሀገሬ ይሄንን ትመስላለች’ የሚሉበት መድረክ ነው። ሀገርን በሚያኮራና ለሌሎች ለመጋበዝ በማያሳፍር መልኩ መገንባት፣ ለቱሪዝም ኢንዱስትሪ መሠረቱ ነው።” ያሉትም የበለጸገች ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ በቁጭት መነሳታቸውን ይገልጻል። ነገን ዛሬ እየሠራች ያለችው ኢትዮጵያ ካላት ላይ ሳትነፍግ የገንዘብም ሆነ የሰው ኃብቷን ቱሪዝም ላይ ስታውል፤ አንድም የኢንዱስትሪውን ዐዋጭነት ብሎም የዜጎቿን በየዘርፉ ዘላቂ ተጠቃሚነት በመገንዘብ ነው። እዚህ ላይ ለሀገር ገቢ በማስገኘት እና የሥራ ዕድል በመፍጠር ዘርፉ የሚያበረክተውን ጥቅም ማጤን ይገባል። በአዲስ አበባ ከተከናወኑ ቁልፍ የቱሪዝም ልማቶች መከካከል፤ የመስቀል ዐደባባይ ቅርስን ማንበርና ማዘመን፣ ከአዲስ አበባ ልማት ጋር ተሣሥሮ የተገነባው የዓድዋ ድል መታሰቢያ፣ በአዲስ መልክ የታደሠው ብሔራዊ ቤተ-መንግሥት፣ የአምሥቱ ዕውቀት ተኮር ማዕከላት (አብርኾት ቤተ-መጻሕፍት፣ ሳይንስ ሙዝየም፣ የሀገር በቀል ዕጽዋት ማሳያ፣ የአንድነት ቤተ-መዛግብት እና የማዕድን ሙዝየም) ግንባታ፣ የአዲስ አበባ ኮንቬንሽን ማዕከል እና ሌሎችም ይገኙበታል። በሌላ በኩል ደግሞ ጎብኚዎች የሚያርፉበት ሎጂና ሆቴሎች ግንባታም በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። ገበታ ለሸገር ብሎ ከአዲስ አበባ የተነሳው የቱሪዝም ልማት በገበታ ለሀገርና ገበታ ለትውልድ ወደ ክልሎች ተስፋፍቶ ደረጃቸውን የጠበቁ ሎጂዎች እንዲገነቡ አስችሏል። የተገነቡት ሎጂዎች ደግሞ ለጎብኚዎቹ ምቾትን የሚያስጠብቁ መሠረተ-ልማቶችን ስበዋል። በርካታ ጎብኚ መሳብና ገቢን ማሳደግ፣ በጎ ገጽታን መሸጥ፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር፣ የበለጸገች ኢትዮጵያ ዕውን ማድረግ እየተከናወኑ ላሉ ተግባራት ሁሉ ግቦች ናቸው። መንግሥት ዕምቅ የጎብኚዎች መስኅብ ዐቅም የሆኑና አቧራ ለብሰው የተደበቁትን ፀጋዎች ውበታቸውን ገላልጦ እያሳዬ ያለውም ለዚህ ነው። ቱሪዝም በቀጥታ ዜጎች (ሰዎች) የሚጠቀሙበት ኢንዱስትሪ ነው። ለዚህ ደግሞ ሰዎች ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠርና መጠበቅ ይኖርባቸዋል።መሠረተ-ልማቶችን በመጠበቅ እንዲሁም ከመንግሥት ጎን በመሆን በሚፈለጉበት ሁሉ ንቁ ተሳትፎ ማድረግም ይጠበቅባቸዋል።
ኢትዮጵያ እና ጣሊያን የ70 ሚሊዮን ዩሮ የብድር ስምምነት ተፈራረሙ
Jun 29, 2026 707
አዲስ አበባ፤ሰኔ 22/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ እና ጣሊያን የ70 ሚሊዮን ዩሮ የብድር ስምምነት ተፈራርመዋል፡፡ ስምምነቱ በረጅም ጊዜ የሚከፈል የብድር ስምምነት ሲሆን ለሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የልማት ሥራዎች ማስፈጸሚያ የሚውል መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገልጸዋል። የብድር ስምምነቱን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ እና በኢትዮጵያ የጣሊያን አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ ተፈራርመውታል። የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አሕመድ ሽዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ይህ የብድር ስምምነት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ጠንካራ አጋርነት የሚያሳይና የረጅም ጊዜ ታሪካዊ ግንኙነታቸውን ይበልጥ የሚያጠናክር ነው። ስምምነቱ ቀደም ሲል በሁለቱ ሀገራት መካከል የተደረሱት የትብብር ማዕቀፎች አካል መሆኑንም ጠቁመዋል። የገንዘብ ድጋፉ ኢትዮጵያ የጀመረቻቸውን ሀገራዊ የኢኮኖሚ ማሻሻያ እርምጃዎችና የልማት ግቦችን ለማሳካት አስተዋፅዖ እንደሚኖረው አስረድተዋል። ኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ተግባራዊ በማድረግ ሁለተኛውን ምዕራፍ በስኬት ማጠናቀቋን ገልጸዋል። ይህንኑ ተከትሎ የዓለም ባንክ ለሶስተኛው ምዕራፍ የሪፎርም ትግበራ የሚውል የበጀት ድጋፍ ማፅደቁንም አስታውሰዋል። የጣሊያን መንግሥት ለኢትዮጵያ የልማት ጥረቶችና የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለሚያደርገው የገንዘብ ድጋፍና ቀጣይነት ላለው አጋርነት ምስጋና አቅርበዋል። አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ የ10 ዓመት መሪ የልማት ዕቅድ እና የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሀገሪቱን በትክክለኛ የዕድገት አቅጣጫ እየመራት መሆኑን ገልጸዋል። መንግስታቸውም ይህንን ሂደት በቁርጠኝነት እንደሚደግፍ አረጋግጠዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን በተግባር ለማገዝ የሚያስችል የ70 ሚሊዮን ዩሮ የብድር ስምምነት ከዓለም ባንክ መርሆዎች ጋር በተጣጣመ መልኩ መፈጸሙን አስታውቀዋል።
በዘንድሮ በጀት አመት ከ7 ሺ 7መቶ በላይ የገጠር ቤተሰቦች ከተረጂነት ወደ አምራችነት ተሸጋግረዋል
Jun 29, 2026 172
ድሬደዋ፣ ሰኔ 22/2018(ኢዜአ)፡- በዘንድሮ በጀት አመት ከ 7 ሺህ 7 መቶ በላይ የገጠር ቤተሰቦች ከተረጂነት ወደ አምራችነት መሸጋገራቸውን የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ አስታወቀ። ተረጂነትን የሚጠየፍ አምራች ማህበረሰብ የማፍራትና በዘርፉ ለተገኙ ውጤቶች እውቅና የመስጠት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ነው የተገለፀው። የቢሮው ምክትል ኃላፊ ሚስራ አብደላ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ ዝናብ አጠር በሆነው በድሬደዋ ገጠራማ አካባቢዎች ማህበረሰቡ ከጠባቂነትና ከተረጂነት ወጥቶ ምርታማ እንዲሆን በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል። ባለፉት አምስት አመታትም በአነስተኛ መስኖ፣ በሌማት ትሩፋት፣ በሰብልና በፍራፍሬ እንዲሁም በተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ የተከናወኑ ተግባራት ህብረተሰቡን ከገጠር ልማታዊ ሴፍትኔት ፕሮግራም ወደ አምራችነት አሸጋግሯል ብለዋል። በተለይም የገጠሩን ክላስተር ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የተከናወኑት ተግባራት ተረጂነት የሚጠየፍ ትውልድ በማፍራት ውጤት እንዲመዘገብበት አድርጓል ነው ያሉት። አርብቶ አደሩ እና አርሶ አደሩ ማሕበረሰብ በተፈጥሮ ሃብቱና በተገነቡት መሰረተ ልማቶች በመታገዝ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የሚያደርገውን ጉዞ ለማሳለጥ እንዳስቻለም ነው የተናገሩት። ለአብነትም ኡሉል ሞጆ የገጠር ቀበሌ ህብረተሰብ ሙሉ በሙሉ ከተረጂነት ወደ አምራችነት መሸጋገሩንም ነው ኃላፊዋ ያነሱት። በዘንድሮው በጀት ዓመትም 7 ሺህ 7መቶ በላይ የገጠር ቤተሰብ ከተረጂነት ወደ አምራችነት መሸጋገራቸውን ገልጸዋል ። በግብርና፣ በአነስተኛ የንግድ ስራዎች ሽግግር ላደረጉት አርሶ እና አርብቶ አደሮች ለስራቸው መቀላጠፍ የመነሻ ካፒታልና ሙያዊ ድጋፍ መደረጉንም አንስተዋል። ከተረጂነት ለተሸጋገሩት የህብረተሰብ ክፍሎች በዚህ ወር መጨረሻ ዕውቅናና ሽልማት እንደሚሰጥም ነው የገለጹት።
የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ ዘርፍ እመርታ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማስፋት ከፍተኛ ጠቀሜታ እያስገኘ ነው - የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር
Jun 29, 2026 158
አዲስ አበባ፤ሰኔ 22/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ ዘርፍ እመርታ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማስፋት ከፍተኛ ጠቀሜታ እያስገኘ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ገለጸ። የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ ልማት አቅጣጫ በግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝምና ዲጂታል ዘርፎች የሀገርን ዕድገት የሚያፋጥን አቅም እየፈጠሩ ይገኛል። የብዝኅ ኢኮኖሚ የልማት አቅጣጫ እመርታዊ ውጤትም ምርታማነትን በማሻሻል፣ ንግድና ኢንቨስትመንትን በማበረታታት ለዜጎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት አስቻይ ሁኔታን ፈጥሯል። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም በከተማና ገጠር የተፈጠረው ከፍተኛ የኢኮኖሚ መነቃቃትም በሁሉም ዘርፍ በርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚእንዲሆኑ እያደረገ ነው። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ እንዳሉት፤ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርሙ ከሀገራዊ ለውጡ በፊት የነበረውን ግብርና መር የኢኮኖሚ ሥርዓት ወደ ብዝኅ ዘርፍ ማሸጋገር አስችሏል። ይህም የኢትዮጵያን የልማት አማራጮች በማስፋትና የዘርፎችን ምርታማነት በማሳደግ የኢኮኖሚ ዕድገትና ተወዳዳሪነትን የሚያሻሽል አቅም እንዲፈጠር እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በብዝኅ ኢኮኖሚ ሥርዓት ግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝምና አይ.ሲ.ቲ. የተፈጠረው እመርታዊ ውጤትም የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማስፋት ከፍተኛ ጠቀሜታ እያስገኘ መሆኑን ተናግረዋል። በሌላ መልኩም ግዙፍ ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች የዜችን የሥራ ዕድል በማስፋት ኢትዮጵያን አፍሪካዊት የብልፅግና ተምሳሌት የማድረግ ርዕይ መሰረት እየጣሉ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የከተሞች ኮሪደር፣ የቱሪዝምና የኢትዮጵያ ታምርት ሀገር አቀፍ ንቅናቄም የዕውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማፋጠን የሚሊዮኖች ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማስፋት ከኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ ዘርፍ የዕድገት አማራጮች ጋር በማጣጣም በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በሚቀጥሉት ሶሰት ዓመታትም በሀገር ውስጥ 16 ሚሊየን ዜጎችን በውጭ ሀገራት ደግሞ 3 ነጥብ 5 ሚሊየን ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተቋቋሙ የግብይት ማዕከላት የተረጋጋ የገበያ ስርዓት ፈጥረዋል
Jun 29, 2026 193
ሆሳዕና ፤ሰኔ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተቋቋሙ የግብይት ማዕከላት አምራቹንና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት የተረጋጋ የገበያ ስርዓት እየፈጠሩ መሆኑን አምራቾችና ሸማቾች ገለፁ። በክልሉ ዱራሜና ወራቤ ከተሞች ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ ሸማቾችና አምራቾች በክልሉ የተቋቁሙ የግብይት ማዕከላት አምራቹንና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት የተረጋጋ የግብይት ስርዓት እየፈጠሩ ነው ብለዋል፡፡ አስተያየታቸውን ከሰጡ ሸማቾች መካከል የዱራሜ ከተማ ነዋሪው ወንድሙ ዋጠሮ በከተማው የተቋቋሙ የግብይት ማዕከላት ሳምንቱን ሙሉ የግብርናና የፋብሪካ ውጤቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ይህም የተረጋጋ ግብይትን በመፍጠር የነጋዴውንም ሆነ የሸማቹን ተጠቃሚነት እያረጋገጡ መሆኑም አክለዋል። በከተማው በእንስሳት እርባታ ዘርፍ የተሰማሩት ካሰች አዎ በበኩላቸው የከተማው የግብይት ማዕከላት የእንስሳት ተዋፅኦዎችን በተመጣጣኝ ዋጋና በቅርበት ለሸማቹ እንዲያቀርቡ ማስቻላቸውን ገልጸዋል። ይህም ምርታቸው ሳይበለሽ በጊዜና የማጓጓዟ ወጪያቸውን በቀነሰ መንገድ ሳምንቱን ሙሉ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከስደት መልስ በጥምር ግብርና ተደራጅታ ስራ መጀመሯን የገለጸችው መኪያ ጀማል በበኩሏ በከተማው የተገነባው ከሰንበት እስከ ሰንበት የግብይት ማዕከል የግብርና ምርታቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጻለች። ከዚህ ቀደም ምርቶቻቸውን ወደ ተለያዩ አካባቢዎች ቦታዎች በማጓጓዝ ለገበያ ለማቅረብ የሚፈጅን ግዜና ተጨማሪ የትራንስፖርት ወጪ መቀነስ እንደቻለች አስታውሳለች፡፡ የግብይት ማዕከሉ አምራቹንና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት በህገወጥ ነጋዴዎችና ደላሎች አማካኝነት በምርት ላይ የሚደረገውን ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ ማስቀረቱን ገልፃለች። የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ባዬሽ ተስፋዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው በክልሉ የህብረተሰቡን የኑሮ ደረጃ ያማከለ አገልግሎት የሚሰጡ ግብይት ማዕከላትን የማስፋት ስራ እየከተናወነ ነው ብለዋል፡፡ በክልሉ ከሚገኙ አጠቃላይ የግብይት ማዕከላት ውስጥ 102 የሚሆኑትን ሳምንቱን ሙሉ አገልግሎት እንዲሰጡ ለማስቻል ማዕከላቱን የማዘመን ስራ እየተሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል። በግብይት ማዕከላቱ ሸማቹንና አምራቹን በማገናኘት በቅናሽ ዋጋ የግብርና፣ የፋብሪካና የኢንዱስትሪ ምርቶች እየቀረቡ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም የማህበረሰቡ ተጠቃሚነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ጠቅሰው የኑሮ ውድነቱን ለመቆጣጠር የሚያስችሉ የግብይት ማዕከላትን የማጠናከር ስራ በልዩ ትኩረት እንደሚሰራም ገልጸዋል።
ፕሮጀክቱ የኢትዮጵያ ምርቶች በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ያላቸውን ተፈላጊነትና ተወዳዳሪነት ይበልጥ ለማሳደግ ትልቅ አቅም ይፈጥራል
Jun 29, 2026 207
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 22/2018 (ኢዜአ):-የብሔራዊ የንግድ ጥራት መሠረተ ልማት ማጠናከሪያ ፕሮጀክት የኢትዮጵያ ምርቶች በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ያላቸውን ተፈላጊነትና ተወዳዳሪነት ይበልጥ ለማሳደግ ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴዔታ እንዳለው መኮንን ገለጹ። በኮሪያ ዓለም አቀፍ የልማት ትብብር ኤጀንሲ (KOICA) የሚደገፈውና የኢትዮጵያን ምርቶች በዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ያላቸውን ተፈላጊነትና ተወዳዳሪነት ይበልጥ የሚያሳድገው "የብሔራዊ የንግድ ጥራት መሠረተ ልማት ማጠናከሪያ ፕሮጀክት" በዛሬው ዕለት በይፋ ተጀምሯል። በፕሮጀክቱ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፣ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ድኤታ አቶ እንዳለው መኮንን፣ የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር መሠረት በቀለ (ዶ/ር) እና የኮይካ (KOICA) ምክትል ፕሬዚዳንት ሺን ስንግ ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ድኤታ አቶ እንዳለው መኮንን በዚሁ ወቅት፤ ፕሮጀክቱ በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የሚተገበር መሆኑን ገልጸዋል። ይህ የሀገሪቱን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ እንዲሁም የውጭ ንግድ ተወዳዳሪነትን በከፍተኛ ደረጃ ለማጠናከር ጉልህ ሚና እንደሚኖረው አስገንዝበዋል። ፕሮጀክቱ የጥራት መሠረተ ልማት ተቋማትን አቅም በመገንባት የላብራቶሪ ምርመራና የደረጃዎች ዝግጅት ሥርዓትን ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀ እንዲሆን እንደሚያስችል ጠቁመዋል። በዚህም የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች በጥራት ለአገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እንዲቀርቡ የቁጥጥርና የምርመራ አቅም ይጎለብታል ብለዋል። አሰራሩ የአገር ውስጥ ምርቶች በዓለም አቀፍ ገበያ ተቀባይነት እንዲያገኙ ከማድረግ ባለፈ፣ ደረጃቸውን ያልጠበቁና ጥራታቸውን ያልጠበቁ ምርቶች በሀገር ውስጥ እንዳይሰራጩ ለመግታት እንደሚያግዝም አመላክተዋል። የኮሪያ ዓለም አቀፍ የልማት ትብብር ኤጀንሲ (KOICA) ምክትል ፕሬዚዳንት ሺን ስንግ በበኩላቸው፤ የተመደበው ድጋፍ በዘርፉ የተሰማሩ የጥራት መሠረተ ልማት ባለሙያዎችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂና አሠራር ለማሰልጠንና ብቃታቸውን ለማሳደግ የሚውል መሆኑን አረጋግጠዋል።
የደረጃ 'ለ' ግብር ከፋዮች ሙሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል ሥርዓት ሊሸጋገሩ ነው
Jun 29, 2026 154
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የደረጃ 'ለ' ግብር ከፋዮችን የሚያስተናግደው የ'eTax' ሥርዓት በ2019 ዓ.ም በጀት ዓመት ሙሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል አገልግሎት አሰጣጥ እንደሚሸጋገር የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ። የአዲስ አበባ ከተማ ገቢዎች ቢሮ የሞደርናይዜሽን ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ መሃመድ አብዱረህማን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ ቢሮው ባለፉት ሁለት ዓመታት የአገልግሎት አሰጣጡን ውጤታማ ለማድረግ በርካታ የሪፎርም ሥራዎችን አከናውኗል። በዚህም ግብር ከፋዮች በአካል ሳይመጡ በኢሜል እና በተዘረጋው የኦንላይን ሊንክ ብቻ አገልግሎቱን ማግኘት እንዲችሉ፣ ከገቢዎች ሚኒስቴር ጋር በመቀናጀት የተቀናጀ የልማት ሥርዓት ተዘርግቶ ወደ ተግባር መግባቱን አመልክተዋል። ይህ አዲስ ዲጂታል አሠራር ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው ምቹ አገልግሎት የሚያገኙበት ምኅዳር የፈጠረ ሲሆን፣ የባለቤትነት ስም ዝውውርን ጨምሮ የተለያዩ የሕግ ተገዥነት አገልግሎቶችንም በውስጡ ያካተተ መሆኑን ምክትል ቢሮ ኃላፊው አስረድተዋል። ከዚህ በተጨማሪም ቢሮው በራሱ አቅም ያለማውን የዕዳ ክትትል ሥርዓት ወደ ተግባር በማስገባቱ፣በ17ቱም ቅርንጫፎች የሚወሰኑ የዕዳ ውሳኔዎችን በቅርበት ለመከታተልና የሚሰበሰበውን ገቢ በፍጥነት ወደ ካፒታል በመለወጥ ረገድ ከፍተኛ አፈጻጸም መመዝገቡን ነው የገለጹት። የክሊራንስ (የግብር ነፃነቱ ማረጋገጫ) አሰጣጥ ሂደቱን ይበልጥ ግልጽ፣ ቀልጣፋና እምነት የሚጣልበት ለማድረግም ባርኮድ (Barcode) ያለው አዲስ የኦንላይን አሠራር ተግባራዊ መደረጉንም እንዲሁ። የተዘረጉት እነዚህ የዲጂታል አገልግሎቶች ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው ግብራቸውን እንዲያሳውቁና እንዲከፍሉ በማስቻላቸው፣ በየወሩ መጨረሻ ላይ በቅርንጫፍ ቢሮዎች ይታይ የነበረውን ከፍተኛ መጨናነቅና የረጅም ጊዜ ጥበቃ ሙሉ በሙሉ ማስቀረት መቻሉን አመልክተዋል። ቢሮው በቀጣዩ በጀት ዓመትም የደረጃ "ለ" ግብር ከፋዮችን የሚያስተናግደውን የኢቲ ታክስ (eTax) ሥርዓት ሙሉ ለሙሉ ወደ ዲጂታል በማሸጋገር፣ ግብር ከፋዮች ካሉበት ሳይንቀሳቀሱ አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችሉ ተጨማሪ ማሻሻያዎችን እንደሚተገብር ጠቁመዋል።
ምክር ቤቱ በመደበኛ ስብሰባው በረቂቅ በጀቱ ላይ መወያየትን ጨምሮ የተለያዩ አዋጆችን ያፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል
Jun 29, 2026 149
አዲስ አበባ፤ሰኔ 22/2018 (ኢዜአ)፦ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 29ኛ መደበኛ ስብሰባውን ነገ ያደርጋል። ምክር ቤቱ በመደበኛ ስብሰባው በፌዴራል መንግስት የ2019 በጀት አመት ረቂቅ በጀት ላይ በዝርዝር እንደሚወያይ ገልጿል። በተጨማሪም ምክር ቤቱ ሦስት ረቂቅ አዋጆችን ማለትም የፌዴራል ታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ፣ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ረቂቅ አዋጅ እና የኢትዮጵያ የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅን አስመልክቶ የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የሚያቀርባቸውን ሪፖርትና የውሳኔ ሀሳቦች መርምሮ አዋጆቹን ያፀጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል።
የሳዑዲ አረቢያ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ለመሠማራት ያላቸውን ፍላጎት ገለጹ
Jun 29, 2026 271
አዲስ አበባ፤ሰኔ 22/2018 (ኢዜአ)፦የሳዑዲ አረቢያ የተለያዩ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ለመሠማራት ፍላጎት እንዳላቸው አስታወቁ። በሳዑዲ አረቢያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ምክትል የሚሲዮን መሪ አምባሳደር አወል ወግሪስ ሙሃመድ የተመራ ከፍተኛ ዲፕሎማሲያዊ ልዑካን ቡድን በደማም ሁለተኛ የኢንዱስትሪ ከተማ የሚገኙትን ጆ ድሪንክስ (Jo Drinks Factory) እና ሶይል ሮስተርስ (Soil Roadsters) ፋብሪካዎችን ጎብኝቷል። በጉብኝቱ ወቅት አምባሳደር አወል ለኩባንያዎቹ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ፣የኢንቨስትመንት ፖሊሲዎች እና የተቀናጁ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮችን (IAIPs) አስመልክቶ ገለጻ አድርገዋል። የጆ ድሪንክስ ኩባንያ ከአልኮል ነፃ የሆኑ መጠጦችን አምራች ሲሆን፣ ኩባንያው በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋዩን ለማፍሰስና ምርቶቹን ለአገር ውስጥ እና ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ፍላጎት እንዳለው አስታውቋል። ሶይል ሮስተርስ ኩባንያ ከኢትዮጵያ የጉጂ፣ ጨልጨሌ፣ ሲዳማ ቦንቤ እና ይርጋጨፌ ልዩ ቡናዎችን (Specialty Coffee) እያስመጣ የሚቆላው ፋብሪካው፤ በቀጣይ በቀጥታ ከኢትዮጵያ አምራቾችና ማህበራት ለመግዛት መወሰኑን ገልጿል። አምባሳደር አወል ወግሪስ የሁለቱ ኩባንያዎች መሪዎች በኢትዮጵያ የቅድመ-ኢንቨስትመንት ጉብኝት እንዲያደርጉ ጋብዘዋል። በሪያድ የሚገኘው ኤምባሲ ለጉብኝቱ አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ እንደሆነ ገልጸዋል። ጉብኝቱ የኢትዮጵያ እና ሳዑዲ አረቢያ ግብርና ኢንዱስትሪን ጨምሮ በንግዱ ዘርፍ ያላቸውን ትብብር ይበልጥ ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
በደቡብ ወሎ ዞን በተያዘው የመኸር እርሻ ከ224 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ ይለማል
Jun 28, 2026 573
ደሴ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):-በደቡብ ወሎ ዞን በምግብ ራስን ለመቻልና የኢንዱስትሪ ግብአት አቅርቦትን ለማሳደግ በመኸር እርሻ ከ224 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ እንደሚለማ የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ይመር ሰይድ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ዞኑ ለስንዴ ሰብል ልማት ምቹ በመሆኑ በተያዘው የመኸር እርሻ ስንዴን በስፋት ለማልማት ዝግጅት ተደርጓል። በዚህም በክረምቱ ከ224 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ በማልማት ከ9 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል ብለዋል። የስንዴ ልማት ምርታማነትን ለማሳደግም ከ400 ሺህ ኩንታል በላይ ሰው ሰራሽ ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑንም ገልጸዋል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ለስንዴ ልማት የተሰጠው ትኩረት አርሶ አደሩን ውጤታማ ከማድረግ ባለፈ በምግብ ራሱን ለመቻልና ለኢንዱስትሪ የሚሆን ግብአት እንዲያቀርብ ማስቻሉንም ተናግረዋል። ስንዴን በሜካናይዜሽን፣ በኩታ ገጠም እና በአዳዲስ አሰራሮች ታግዞ ማምረት መቻሉ እየተገኘ ላለው ውጤት መሰረት መሆኑንም አመልክተዋል። በዞኑ ጀማ ወረዳ የቀበሌ 08 ነዋሪ አርሶ አደር እንድሪስ አበበ በሰጡት አስተያየት እንዳሉት፣ ሁለት ሄክታር መሬታቸውን በስንዴ ለማልማት ማሳቸውን ደጋግመው በማረስ ለዘር ሥራ አዘጋጅተዋል። በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ ታግዘው በማልማትና የሰብል እንክብካቤ ሥራ በማከናወን እስከ 90 ኩንታል ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውንም ገልጸዋል። በዘንድሮው የመኸር ወቅት አንድ ሄክታር ተኩል ማሳቸው ላይ ስንዴ ለማልማት እንደተዘጋጁ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በወረኢሉ ወረዳ የቀበሌ 04 ነዋሪ አርሶ አደር አህመድ ታደሰ ናቸው። ቀደም ሲል ለስንዴ ልማት ብዙም ትኩረት እንደማይሰጡ አስታውሰው፣ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ስንዴን ማልማት ባህል በማድረጋቸው ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። ባለፈው ዓመት በመኸር ወቅት በስንዴ ከለማው 200 ሺህ ሄክታር መሬት ከ6 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን ለማወቅ ተችሏል።
በኦሮሚያ ክልል ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል
Jun 28, 2026 519
አዳማ ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):-በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ በተከናወኑ የልማትና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴዎች ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል መፍጠር ተችሏል። በኦሮሚያ ክልል ከ3 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገብ የቻሉ 1 ሺህ 195 የሚሆኑ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን ወደ ላቀ የኢንቨስትመንት ደረጃ የማሸጋገር ፕሮግራም በአዳማ ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የጨፌ ኦሮሚያ የከተማ ልማት ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አብዱልቃድር ሁሴን እንደገለጹት፤ ኢንተርፕራይዞቹ ከመንግሥት የተሰጣቸውን ዘርፈ-ብዙ ድጋፎችና ምቹ ፓኬጆችን በአግባቡ ወደ ተግባር በመቀየር ለዚህ ስኬትና የሽግግር ደረጃ በቅተዋል። የክልሉ መንግሥት ድህነትን ለመቀነስ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዲሁም የስራ አጥነት ችግርን በዘላቂነት ለመቅረፍ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩ ኢንተርፕራይዞች ባስመዘገቧቸው ስኬቶች ሳይዘናጉ፣ ይበልጥ ለላቀ ውጤት ለመብቃት በሚሰማሩበት የኢንቨስትመንት መስክ ላይ ጠንክረው መስራት እንዳለባቸውም አቶ አብዱልቃድር አስገንዝበዋል። የኦሮሚያ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ኤባ ገርባ በበኩላቸው፤ ኢንተርፕራይዞቹ በተሰማሩባቸው የሥራ መስኮች ውጤታማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት ደረጃ መሻገራቸውን ገልጸዋል። በተጨማሪም በመጠናቀቅ ላይ ባለው የበጀት ዓመት ብቻ ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አዲስ የሥራ ዕድል ማመቻቸት መቻሉን ኃላፊው ይፋ አድርገዋል። ኃላፊው አክለውም፤ ወደ ሥራ ለገቡ ዜጎች ከ40 ቢሊዮን ብር በላይ የብድር አቅርቦት መሰራጨቱንና ከ10 ሺህ በላይ የሊዝ ማሽነሪዎችም ለኢንተርፕራይዞቹ መሰጠታቸውን ጠቅሰዋል። ለሥራ አጥ ዜጎች ከተፈጠሩት የሥራ ዕድሎች መካከል የጎጆ ኢንዱስትሪ፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ንግድ፣ ግብርና፣ አገልግሎት፣ ግንባታ እንዲሁም የብረታ ብረትና የእንጨት ሥራ በዋናነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ገልጸዋል። በተመሳሳይ በበጀት ዓመቱ ከ200 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የክልሉ ዜጎች የውጭ ሀገር የሥራ ዕድል ማመቻቸት መቻሉን ገልጸዋል። ወደ ሥራ ለገቡ ዜጎች የመሥሪያና መሸጫ ቦታዎች እንዲሁም ማዕከላት መተላለፋቸውን የገለጹት ኢንጂነር ኤባ፤ በዚህም ድህነትን በመቀነስ ረገድ ወሳኝ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። የአዳማ ከተማ ምክትል ከንቲባ ማቲያስ ሰቦቃ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ በከተማዋ ሥራ አጥነትን ለመቀነስና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ዘርፈ-ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በአዳማ በጎጆ ኢንዱስትሪ፣ በከተማ ግብርና በተለይም በዶሮ እርባታ፣ በወተት ላሞች ማድለብና በሰብል ልማት ዘርፎች ለሺዎች ለሚቆጠሩ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያን ጂኦ-ስትራቴጂክ ተጠቃሚነት ለማስጠበቅ የድንበርና የኤርፖርት ደኅንነቶችን ማዘመን ወሳኝ ጉዳይ ነው
Jun 28, 2026 800
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያን ጂኦ-ስትራቴጂክ ተጠቃሚነት ለማስጠበቅ የድንበርና የኤርፖርት ደኅንነቶችን ማዘመን ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራልና የኤርፖርትና ድንበር አስተዳደር ትራንስፎርሜሽን ፕሮግራም ዐቢይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ገለጹ። የተቀናጀ የኤርፖርት እና የድንበር አስተዳደር ትራንፎርሜሽን ፕሮግራም ላይ ያተኮረ የምክክርና የግብዓት ማሰባሰቢያ መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራልና የኤርፖርትና ድንበር አስተዳደር ትራንስፎርሜሽን ፕሮግራም ዐቢይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን በዚሁ ወቅት፤ የትራንስፎርሜሽን ፕሮግራሙ የኢትዮጵያን የደኅንነት ስጋቶች አስቀድሞ ለመከላከል፣ የሳይበር ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና በዲጂታል ዘመን ኢትዮጵያ ያላትን ተወዳዳሪነት ለማስቀጠል ወሳኝ ነው ብለዋል። ፕሮግራሙም ስጋቶችን በመረጃ አስደግፎ ለማወቅና ለመከላከል እንዲሁም በተቋማት መካከል የመረጃ ልውውጥን በማሳደግ ሽብርተኝነት፣ ሕገ-ወጥ የሰዎች፣ የገንዘብና የመሣሪያ ዝውውርን በጋራ ለመመከት አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ፕሮግራሙ ሀገር በቀል ቴክኖሎጂዎች እንዲለሙ በማድረግ የሳይበር ሉዓላዊነትን በማረጋገጥና አሰራሮች በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) እና በሰለጠነ የሰው ኃይል እንዲደገፉ ግብ የጣለ መሆኑንም አስረድተዋል። ለዚህም ስኬት የተዘጋጀው ፍኖተ-ካርታ የሚያስፈልጉትን የቴክኖሎጂ አቅም፣ የአሠራር ሥርዓቶች ስታንዳርድ፣ የሰው ሀብት፣ የመሠረተ-ልማት አቅርቦት እንዲሁም የሕግና የቁጥጥር ጉዳዮችን ለይቶ ማስቀመጡንም አብራርተዋል። ፕሮግራሙ የሀገሪቱን የጂኦ-ስትራቴጂክ ቁመና ለማስጠበቅና የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አንዱ ማስፈጸሚያ መሣሪያ እንደሆነ ገልጸዋል። የኢትዮጵያን ጂኦ-ስትራቴጂክ ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ የድንበርና የኤርፖርት ደኅንነቶችን ማዘመን እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። በዚህም ሀገሪቱን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሚያደርግ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ፍኖተ-ካርታው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ግቦችን ታሳቢ ያደረገ ሲሆን፣ ሀገሪቱ በቀጣይ ለምታስተናግደው ዓለም አቀፍ ኮንፈረንስ ስኬት ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል። በመድረኩ ላይ ከፍተኛ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የጸጥታ ተቋማት መሪዎች ተገኝተዋል።
የቦንጋ ከተማን እድገትና ልማት በማፋጠን ለነዋሪቿ ምቹ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jun 28, 2026 441
ቦንጋ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):- የቦንጋ ከተማን ዕድገትና ልማት በማፋጠን ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የካፋ ዞን አስተዳደር አስታወቀ። የከተማ አስተዳደሩ ለቀጣይ አሥር ዓመታት ተግባራዊ የሚያደርገው የቦንጋ ከተማ ስትራክቸራል ማስተር ፕላን ላይ ያተኮረ የሕዝብ ውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል። ይህ አዲስ ስትራክቸራል ፕላን የከተማዋን የመሠረተ ልማት አቅርቦት፣ የመኖሪያ ቤት ፍላጎት፣ የአረንጓዴ ስፍራዎችን አጠባበቅ እና የኢንዱስትሪ ቀጠናዎችን በዘመናዊ መንገድ ለመምራት የተነደፈ መሆኑም ተገልጿል። ዕቅዱ በቀጣይ አሥር ዓመታት ከተማዋን በፕላን በመምራት በዘፈቀደ የሚደረጉ ግንባታዎችን ለመግታትና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥ ለመዘርጋት ትልቅ መሠረት ይጥላል ተብሎም ይጠበቃል። በመድረኩ ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ፤ የቦንጋ ከተማ ረጅም ዓመታትን ያስቆጠረች እድሜ ጠገብ ከተማ መሆኗን ተናግረዋል። ከተማዋ ታሪኳን በሚመጥን መልኩ ሳታድግ መቆየቷን ያነሱት ዋና አስተዳዳሪው፤ አሁን ላይ መንግሥት ለከተሞች ዕድገት ከሰጠው ልዩ ትኩረት በመነሳት፣ የቦንጋን ዕድገት በማፋጠን ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የከተማዋን ፕላን በአዲስ መልክ ማዘጋጀት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ፣ ከኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ ጋር ውል በመግባት ሰፊ ጥናትና ምርምር ሲደረግ መቆየቱን ዋና አስተዳዳሪው ገልጸዋል። ፕላኑ ላይ ከዚህ ቀደም የተለያዩ የውይይት መድረኮች ሲደረጉ መቆየታቸውን የገለጹት ዋና አስተዳዳሪው፤ በዛሬው የሕዝብ መድረክ ላይ የሚሳተፉ የኅብረተሰብ ክፍሎችም አስፈላጊውን ሐሳብና አስተያየት በመስጠት ለከተማዋ ዕድገትና ልማት የድርሻቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። ቦንጋ ከተማ ደረጃዋን የጠበቀችና ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትሆን በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የቦንጋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተክለአብ ቡሎ(ዶ/ር) የገለጹ ሲሆን፤ አዲሱ ማስተር ፕላንም ለዚህ ስኬት ትልቅ ድርሻ እንደሚኖረው አስታውቀዋል። አዲሱ ስትራክቸራል ፕላን የአካባቢውን ሥነ-ምህዳር መሠረት ያደረገ መሆኑን የጠቀሱት ከንቲባው፤ ከተማዋን ለልማት፣ ለመኖሪያ ቤት፣ ለንግድና ለኢንቨስትመንት ምቹ ከማድረግ ባለፈ የገቢ አቅሟን የሚያሳድግ መሆኑንም ጠቁመዋል። ከዚህም ባሻገር ፕላኑ ለሕብረተሰቡን የረጅም ጊዜ የመልማት ፍላጎት ምላሽ የሚሰጥ መሆኑን ከንቲባው ገልጸው፤ አሁን እየተካሄደ ያለው ውይይት አስፈላጊ ግብዓቶችን በማካተት ፕላኑ በተሟላ መልኩ እንዲተገበር ከፍተኛ ሚና እንዳለው ተናግረዋል። ለሚቀጥሉት አሥር ዓመታት የሚያገለግለው ይህ አዲስ ፕላን፤ የከተማዋን ነባር 6 ሺህ 300 ሄክታር ስፋት ወደ 15 ሺህ ሄክታር በላይ ያሳደገ መሆኑ በውይይቱ ላይ ተመልክቷል። በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮችና የተለያዩ ህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
በኦሮሚያ ክልል የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ የተጠናከረ የሰብል ጥበቃ ሥራ በቅንጅት እየተከናወነ ይገኛል
Jun 28, 2026 297
አዳማ ፤ ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀናጀ የሰብል ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የ2018/19 የምርት ዘመን የሰብልና ፍራፍሬ ጥበቃና እንክብካቤ ላይ ያተኮረ የንቅናቄ መድረክ በአዳማ ከተማ በማካሄድ ላይ ይገኛል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ በሪሶ ፈይሳ በወቅቱ፤ በክልሉ ግብርናውን ለማዘመንና ውጤታማ ለማድረግ የተነደፉት ኢኒሼቲቮች አርሶ አደሩንና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ችለዋል። ለዚህ ስኬት ደግሞ የሰብል ጥበቃና እንክብካቤ፣ የግብዓት አቅርቦት፣ የአፈር ለምነት አጠባበቅ እንዲሁም የባለሙያ ድጋፍ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማበርከታቸውን ምክትል ኃላፊው አንስተዋል። በተጨማሪም የሰብል ልማትን በሽፋንም ሆነ በምርታማነት ዘላቂ ለማድረግ ከግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝም አክለው ገልጸዋል። የሰብል ምርትና ምርታማነትን የሚጎዱ አረም፣ ተባይና በሽታዎችን በአስተማማኝ ሁኔታ ለመቆጣጠር ሳይንሳዊ መንገዶች ተግባራዊ እየተደረጉ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዛሬው የንቅናቄ መድረክም የዘርፉ አመራሮችና በየደረጃው የሚገኙ የሰብል እንክብካቤ ባለሙያዎች ይህንኑ ስኬት በጋራ ለማሳካት እንዲረባረቡ ለማስቻል ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። ከሰብል ጥበቃው በተጨማሪ፣ አሲዳማነታቸው የጨመረና ምርታማነታቸው የቀነሰ መሬቶችን በኖራና በተፈጥሮ ማዳበሪያ በማከም ረገድ ሰፊ ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል። የቢሮው የሰብል እንክብካቤ ኃላፊ አቶ ደጀኔ ሂርጳ በበኩላቸው፤ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ከግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ምርምር ማዕከላቱ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በሽታን የሚቋቋሙ ዝርያዎችን በምርምር በማፍለቅ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግና ሙያዊ እገዛ የመስጠት ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን ለአብነት ጠቁመዋል። ለዚህም ከዘር በፊት የሚደረግ የማሳ ዝግጅት ላይ ትኩረት የተሰጠ ሲሆን፣ ቡቃያውን ከአረሞች፣ ተባዮችና በሽታዎች ቀድሞ መለየትና መከላከል ላይ በቅንጅት በመስራት ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ በየደረጃው የሚገኙ የዘርፉ አመራሮች፣ ባለሙያዎች እና የግብርና ምርምር ማዕከላት ኃላፊዎች ተሳታፊ ሆነዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአፍሪካ ምርጥ የአየር ጭነት አጓጓዥ አየር መንገድ ሽልማትን አሸነፈ
Jun 28, 2026 307
አዲስ አበባ፤ሰኔ 21/2018 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአፍሪካ ምርጥ የአየር ጭነት አጓጓዥ አየር መንገድ ሽልማትን አሸንፏል። አየር መንገዱ ሽልማቱን ያገኘው የኢትዮጵያ ካርጎ እና ሎጂስቲክስ አገልግሎት በ2026ቱ የእስያ ጭነት፣ ሎጂስቲክስ እና አቅርቦት ሰንሰለት የሽልማት ስነ ስርዓት ላይ ነው። በዚህም የአፍሪካ ምርጥ የአየር ጭነት አጓጓዥ አየር መንገድ በመባል ተሸላሚ ሆኗል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን በጠበቁ መሰረተ ልማቶች፣ ስልታዊ ጥምረቶች፣እንዲሁም አዳዲስ የሎጂስቲክስ አሰራሮች በመታገዝ ዓለም አቀፍ የሎጂስቲክስ እና የንግድ ግንኙነቶችን በማጠናከር ላይ እንደሚገኝም ገልጿል። አየር መንገዱ የካርጎ ሽልማቱን ያገኘው በዘርፉ ባለድርሻ አካላትና በደንበኞች በተሰጠ ከፍተኛ ድምፅ መሆኑን አመልክቷል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ይህ ስኬት ዕውን እንዲሆን ላስቻሉ አጋሮች፣ደንበኞች እንዲሁም ሰራተኞች ምስጋና አቅርቧል፡፡
ቢሮው ተግባራዊ ያደረጋቸው በቴክኖሎጂ የተደገፉ አዳዲስ አሠራሮች የአገልግሎት አሰጣጡን ከማዘመን ባለፈ የከተማዋን የገቢ አቅም አሳድጓል
Jun 27, 2026 812
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ ገቢዎች ቢሮ ተግባራዊ ያደረጋቸው በቴክኖሎጂ የተደገፉ አዳዲስ አሠራሮች የአገልግሎት አሰጣጡን ከማዘመን ባለፈ የከተማዋን የገቢ አቅም ማሳደጉን አስታወቀ፡፡ ቢሮው ቀደም ሲል ግብር ከፋዮች በአካል በመቅረብና የወረቀት ሰነዶችን በመያዝ ያገኙት የነበረውን አገልግሎት ሙሉ ለሙሉ ወደ ኦንላይን ሥርዓት ማሸጋገር ችሏል። የአዲስ አበባ ከተማ ገቢዎች ቢሮ የሞደርናይዜሽን ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ መሃመድ አብዱረህማን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ ቢሮው ባለፉት ሁለት ዓመታት በርካታ የሪፎርም ሥራዎችን አከናውኗል። ግብር ከፋዮች በአካል ሳይመጡ በኢሜል እና በተዘረጋው የኦንላይን ሊንክ አገልግሎቱን ማግኘት እንዲችሉ ከፌደራል ገቢዎች ሚኒስቴር ጋር በመቀናጀት የተቀናጀ የልማት ሥርዓት ተዘርግቶ ወደ ተግባር መገባቱን ጠቁመዋል። ይህ አዲስ አሠራር ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው አገልግሎት የሚያገኙበት ምኅዳር የፈጠረ ሲሆን፣ የባለቤትነት ስም ዝውውርን ጨምሮ የተለያዩ የሕግ ተገዥነት አገልግሎቶችን ያካተተ መሆኑን አስረድተዋል። ቢሮው በራሱ አቅም ያለማውን የዕዳ ክትትል ሥርዓት ወደ ተግባር በማስገባቱ በ17ቱም ቅርንጫፎች የሚወሰኑ የዕዳ ውሳኔዎችን በቅርበት ለመከታተልና የሚሰበሰበውን ገቢ ወደ ገንዘብ በመለወጥ ረገድ ከፍተኛ አፈጻጸም ተመዝግቧል። የክሊራንስ አሰጣጥ ሂደቱን ይበልጥ ግልጽ፣ ቀልጣፋና እምነት የሚጣልበት ለማድረግ ባርኮድ ያለው አዲስ የኦንላይን አሠራር ተግባራዊ መደረጉንም ተናግረዋል፡፡ የተዘረጉት የዲጂታል አገልግሎቶች ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው ግብራቸውን እንዲያሳውቁና እንዲከፍሉ በማድረጉ፣ በየወሩ መጨረሻ ላይ በቅርንጫፍ ቢሮዎች ይታይ የነበረውን ከፍተኛ መጨናነቅና የረጅም ጊዜ ጥበቃ ማስቀረት መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡ ቢሮው በቀጣዩ በጀት ዓመትም የደረጃ "ሐ" ግብር ከፋዮችን የሚያስተናግደውን የኢቲ ታክስ (eTax) ሥርዓት ሙሉ ለሙሉ ወደ ዲጂታል በማሸጋገር፣ ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችሉ ማሻሻያዎችን እንደሚተገብር ገልጸዋል። በከፍተኛ ግብር ከፋዮች ቅርንጫፍ የኤሌክትሮኒክስ ታክስ ግብይት ድጋፍና ክትትል የሥራ ሂደት ተወካይ አቶ ሰይድ መሃመድ፤ ለግብር ከፋዮች ስለ አገልግሎቱ አጠቃቀም በቂ ስልጠናና ተከታታይ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የቅርንጫፉ የኤሌክትሮኒክስ ታክስ ክፍያ አሰባሰብና ክትትል ቡድን አስተባባሪ ተወካይ አቶ ኢድሪስ መሃመድ በበኩላቸው፣ አዲሱ የዲጂታል ሥርዓት ተቋማዊ አፈጻጸምን ከማሳደግና ሥራዎችን ከማቅለል አንጻር ሰፊ ፋይዳ እንዳለው አብራርተዋል። የቅርንጫፉ ተገልጋዮችም በአዲሱ አሠራር መደሰታቸውን ገልጸዋል፡፡ አቶ ታምራት አብራሃም በሰጡት አስተያየት አዲሱ የኦንላይን ሥርዓት ረጅም ሰልፍን ያስቀረና ተገልጋዩ በቤቱ ሆኖ ሁሉንም አገልግሎት ማግኘት እንዲችል ያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አዲሱ አሠራር በሥራቸውና በድርጅታቸው ላይ ዘርፈ-ብዙ ጥቅሞችን እንዳስገኘላቸው የገለጹት ደግሞ አቶ ሙልጌታ ተሻለ ናቸው፡፡ አቶ እስጢፋኖስ ብርሃኔ በበኩላቸው የዲጂታል አሠራሩ ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲያገኙ በማስቻል ይደርስባቸው የነበረውን ከፍተኛ እንግልት ሙሉ በሙሉ ማስቀረቱን ገልጸዋል።