ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
መንግስት የህዝብን የልማት ጥያቄ እየመለሰ ነው - አቶ ሽመልስ አብዲሳ
Feb 5, 2026 101
ሻኪሶ፤ ጥር 28/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት የህዝብን የልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ እየመለሰ እንደሚገኝ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ ተናገሩ፡፡ በሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ድጋፍ የሚገነባው የሻኪሶ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ በተገኙበት የግንባታ ስራ ተጀምሯል፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት መንግስት የህዝብን የልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ እየመለሰ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ዛሬ የግንባታ ስራው የተጀመረው የሻኪሶ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክትም አካባቢው በቡና፣ በማዕድናትና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት የህዝብን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ከሚሰራቸው ተግባራት መካከል ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። የአውሮፕላን ማረፊያው መገንባት የአካባቢውን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የሚያሳልጥ መሆኑንም ገልፀዋል፡፡ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ አካባቢውን ለማልማት ላደረገው ዕገዛ ያመሰገኑት አቶ ሽመልስ፤ የአውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክቱን በአጭር ጊዜ አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት ርብርብ እንደሚደረግ ጠቁመዋል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው፤ አየር መንገዱ አዲስ አበባን ከሀገር ውስጥ ከተሞች ጋር የሚያገናኙ በርካታ በረራዎች እንዳሉት ጠቁመዋል። የሻኪሶ አውሮፕላን ማረፊያም ተጨማሪ የአየር መንገዱ መዳረሻ በማድረግ የጉጂ ዞን የተፈጥሮ ሀብትን ለማልማት ተደማሪ አቅም እንደሚሆን አስረድተዋል። ፕሮጀክቱ ተጠናቆ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ሲጀመር የአካባቢውን ኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለማቀላጠፍና የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ የራሱ ድርሻ እንዳለው ጠቁመዋል፡፡ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፤ ከዚህ በፊት በስፍራው የአውሮፕላን መንደርደሪያ እንደነበር አስታውሰው የክልሉ መንግስት የአውሮፕላን መንደርደሪያውን ወደ ንግድ አውሮፕላን ማረፊያነት ለመቀየር ያቀረበውን ጥሪ በመቀበል ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ግንባታውን ማስጀመሩን ገልፀዋል፡፡ ፕሮጀክቱ ተጠናቆ በተያዘለት ጊዜ አገልግሎት እንዲጀምርም የሚጠበቅባቸውን ሁሉ እንደሚያደርጉ ቃል ገብተዋል፡፡ የሻኪሶ አውሮፕላን ማረፊያ በ124 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ላይ የሚገነባ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡ በይፋዊ የግንባታ ማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳን ጨምሮ የፌዴራል፣ የክልልና የጉጂ ዞን አመራሮች እንዲሁም አባገዳዎች ተገኝተዋል፡፡
በቡና ዘርፍ የተከናወኑ የፖሊሲ ማሻሻያዎች ለውጭ ምንዛሬ ገቢ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል
Feb 5, 2026 64
አዲስ አበባ፤ ጥር 28/2018(ኢዜአ)፦ በቡና ዘርፍ የተከናወኑ የፖሊሲ ማሻሻያዎች ለውጭ ምንዛሬ ገቢ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ከምስራቅ አፍሪካ ፋይን ኮፊ ማህበር (AFCA) ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 22ኛው የአፍሪካ ፋይን ኮፊ (Africa Fine Coffee) ኤግዚቢሽንና ኮንፍረንስ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። ጥር 28 ቀን 2017 ዓ.ም በጀመረው በዚህ መድረክ ላይ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር)፣ የዘርፉ ተመራማሪዎችና ዓለም አቀፍ እንግዶች ተገኝተዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ኢትዮጵያ በ2017 በጀት ዓመት 469ሺህ ቶን ቡና ለዓለም ገበያ በመላክ 2 ነጥብ 65 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን ገልጸዋል፡፡ ይህ ውጤት በሀገሪቱ የቡና ታሪክ ከፍተኛው የገቢና የጥራት መጠን ሆኖ መመዝገቡን ጠቅሰው፤ በያዝነው ዓመት የሚገኘውን ገቢ ወደ 3 ቢሊዮን ዶላር ለማሳደግ ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለቡና ዘርፉ ዕድገት ትልቅ ድርሻ ማበርከቱንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ካለው የዓረቢካ ቡና ዝርያ 90 በመቶ የሚሆነውን የጄኔቲክ ብዝሃ-ህይወት በመያዟ ለዓለም የቡና ኢንዱስትሪ እንደ ዘር ባንክ እንደምትቆጠርም ተናግረዋል፡፡ ይህም ለተለዋዋጭ የአየር ንብረት የማይበገሩ ዝርያዎችን ለማምረት ልዩ ዕድል መፍጠሩን ተናግረው፤ ጥሬ ቡናን ከመላክ ባለፈ እሴት የተጨመረበት ቡናን ወደ ውጭ ለመላክ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጠና አማካኝነት በአህጉሪቱ ውስጥ የቡና ንግድን ለማጠናከር የፖሊሲ ማሻሻያዎች እየተደረጉ መሆናቸውንም እንዲሁ፡፡ የቡናና ሻይ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሻፊ ዑመር፤ መንግስት በቡናው ዘርፍ የጀመረው የሪፎርም ስራ አስደናቂ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል ብለዋል። ይህ የለውጥ እርምጃ ከአምራች አርሶ አደሩ ጀምሮ በንግድ ሰንሰለቱ ውስጥ ያሉ አካላትን ተጠቃሚነት በእጅጉ ማሳደጉን ገልጸዋል። እየተካሄደ የሚገኘው ጉባኤ አፍሪካ የተፈጥሮ ሀብቷን ተጠቅማ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን የቡና ገበያ ድርሻ እንድታሳድግ መልካም አጋጣሚ እንደሚፈጥር አስገንዝበዋል። የአፍካ (AFCA) ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ጊልበርት ጋታሊ በዚሁ ጊዜ በአፍሪካ የቡና ዘርፍን ለማዘመንና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቱን ለማረጋገጥ ከአጋር ድርጅቶች ጋር የተቀናጀ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በተጨማሪም ለላኪዎች፣ ለገዢዎች፣ ለማሽን አምራቾች፣ ለቡና ጥራት ባለሙያዎች እና በጥቅሉ በዘርፉ ኢንዱስትሪው የአቅርቦትና የእሴት ሰንሰለት ውስጥ ላሉ አካላት ሰፊ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ጥረት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። ኤግዚቢሽንና ኮንፍረንሱ ከዘርፉ ተዋናዮች ጋር ጠንካራ ትስስር በመፍጠር የአፍሪካን የቡና ኢንዱስትሪ ለማሳደግ ትልቅ አቅም እንደሚሆን አመልክተዋል።
የግብርና ዘርፉን በማዘመንና ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት ለመውጣት የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው
Feb 5, 2026 62
ወላይታ ሶዶ ፤ ጥር 28/2018(ኢዜአ)፦ የግብርና ዘርፉን በማዘመንና ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት ለመውጣት የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ ግብርና ስራዎች ኮርፖሬሽን አስታወቀ። የኢትዮጵያ ግብርና ስራዎች ኮርፖሬሽን የግብርና ግብዓት ስርጭትን አስመልክቶ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በወላይታ ሶዶ ከተማ የምክክር መድረክ አካሂዷል። በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈፃሚ የሺእመቤት ነጋሽ፤ የግብርና ዘርፉን በማዘመንና ሜካናይዜሽንን ከማስፋት ባለፈ የግብአት አቅርቦቶችን በማሟላት ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት የመውጣት ግብን ለማሳካት የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ኮርፖሬሽኑ ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ እንዲሁም ሌሎች ግብአቶችን በብዛትና በጥራት በማቅረብ የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም መሰረት በበጀት ዓመቱ 2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሮች ለማቅረብ የተሟላ ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል። እስከአሁኑ ሂደት 560 ሺህ ሜትሪክ ቶን ማዳበሪያ ለተጠቃሚዎች መድረሱን ጠቅሰው በዘርፉ ልማት የተያዘውን ግብ ለማሳካት በተደመረ አቅም መስራቱ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በበጀት ዓመቱ ለምርጥ ዘር አቅርቦትም ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ዋና ስራ አስፈፃሚዋ ተናግረዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የግብርና ግብዓት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ግዳልቅ አልቅሚ፤ ኮርፖሬሽኑ የሚያቀርበው ግብዓት በክልሉ የግብርና ሴክተር የተያዘውን ግብ ለማሳካት ትልቅ አቅም መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ለዘርፉ ልማት ስኬታማነት ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት መስራትና ውጤት ማምጣት ይጠበቅበታል ብለዋል። በኦሮሚያ ክልል ግብርና ግብዓቶች ምርት ጥራትና ቁጥጥር የሻሸመኔ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሚደቅሳ ጀቤሳ፤ በኮርፖሬሽኑ በኩል የግብዓት ስርጭት መኖሩ በጥራትና ምርታማነት ላይ ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል። ከኮርፖሬሽኑ ጋር ባለ ጠንካራ የትብብር ግንኙነት የዘር ጥራት ቁጥጥር በማድረግ የተሻለ ውጤት ማምጣት መቻሉን አንስተው በዚህም የአርሶ አደሩ ምርትና ምርታማነት እያደገ መሆኑን ተናግረዋል።
የሌማት ትሩፋት መንግስት ለዜጋ እና ለሀገር ያለውን ክብር ያሳየበት ልዩ እሳቤ እና ትግበራ ነው
Feb 5, 2026 60
አዲስ አበባ፤ ጥር 28/2018 (ኢዜአ)፡-የሌማት ትሩፋት መንግስት ለዜጋ እና ለሀገር ያለውን ክብር ያሳየበት ልዩ እሳቤ እና ትግበራ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ መንግስት በሌማት ትሩፋት ዘላቂ የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ፖሊሲ ትግበራ ተደማሪ አቅም በማድረግ ሰርቷል ብለዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የምዕናብ ልህቀት ፈልቆ የተጀመረው ኢኒሼቲቭ የብዙ ቤተሰብን ሕይወት ቀይሯል፣ ደግሞም ወደፊትም መቀየሩን ይቀጥላልም ሲሉ ጠቁመዋል፡፡ የሌማት ትሩፋት ለዘመናት ጸጋ ሆነው ያልታዩ ጓሮዎችን የልማት ከባቢ አድርጓል፡፡ በመሆኑም የተመጣጠነ ምግብ በሽታ መከላከልን ካስቀደመው የጤና ፖሊሲያችን ጋር ግንኙነቱ ቀጥተኛ ነው፡፡ በዚህም የመደመር እሳቤ ባፈለቀው የፈጠራ ተግባር የእንስሳት ተዋጽኦ በአግባቡ ወደ ሌማታችን አምጥቷል፡፡ የሌማት ትሩፋት የተሳሰረው ከከበረ የሰዎች ከሕይወት እና ጤና እንዲሁም ከትልቁ የሃገር መልክ እና ክብር ብሎም ከዘላቂ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ርዕያችን ጋር ነው ያሉት አቶ ተመስገን፥ በትጋት የሚሰሩ ክንዶች ሌማታቸውን አትረፍርፈዋል ወደፊትም ያትረፈርፋሉ በማለት በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ እና የተመድ የቱሪዝም ድርጅት ኢትዮጵያ ኢኮ ቱሪዝምን ለማስፋት እያከናወነችው ባለው ተግባራት ዙሪያ መከሩ
Feb 5, 2026 88
አዲስ አበባ፤ ጥር 28/2018 (ኢዜአ)፦ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀስላሴ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት(UN Tourism) ዋና ፀሐፊ ሸይካ አል ኖዊስ ጋር ኢትዮጵያ ኢኮ ቱሪዝምን ለማስፋት እያከናወነችው ባለው ተግባራት ዙሪያ መክረዋል። በውይይቱ ኢትዮጵያ የኢኮ ቱሪዝም መዳረሻዎችን ለማስፋት እያከናወነች ያለው ስራ የሚደነቅ መሆኑን የድርጅቱ ዋና ፀሐፊ ሸይካ አል ኖዊስ ገልጸዋል። ውይይቱ ኢትዮጵያ እና ድርጅቱ በአቅም ግንባታ፣ ዘላቂ በሆኑ ኢንሼቲቮችና የፋይናንስ ሀብት አቅርቦት ላይ ያላቸውን ትብብር ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ያተኮረ መሆኑ ተመላክቷል። ዋና ፀሐፊዋ ኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃን ከግምት በማስገባት የኢኮ ቱሪዝም መዳረሻዎችን ለማስፋትና ለማሳደግ እያከናወነች ያለውን ስራ ማድነቃቸውን ኢዜአ ከፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። በፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ የተመራ ልዑክ በዱባይ እየተካሄደ ባለው የ2026 የዓለም መንግስታት ጉባኤ ላይ እየተሳተፈ ይገኛል።
የቡና ወጪ ንግድን ይበልጥ ለማሳደግ እሴት የተጨመረባቸውን ምርቶች ለውጪ ገበያ ለማቅረብ ትኩረት ተደርጓል
Feb 5, 2026 87
አዲስ አበባ፤ ጥር 28/2018(ኢዜአ)፦ የቡና ወጪ ንግድን ይበልጥ ለማሳደግ እሴት የተጨመረባቸውን ምርቶች ለውጪ ገበያ ለማቅረብ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ከምስራቅ አፍሪካ ፋይን ኮፊ ማህበር (AFCA) ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 22ኛው የአፍሪካ ፋይን ኮፊ (Africa Fine Coffee) ኤግዚቢሽንና ኮንፍረንስ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ኢትዮጵያ በ2017 በጀት ዓመት 469ሺህ ቶን ቡና ለዓለም ገበያ በመላክ 2 ነጥብ 65 ቢሊየን ዶላር ገቢ ማግኘቷን ገልጸዋል፡፡ ይህ ውጤት በሀገሪቱ የቡና ታሪክ ከፍተኛው የገቢና የጥራት መጠን ሆኖ መመዝገቡን ጠቅሰው በያዝነው ዓመት የሚገኘውን ገቢ ወደ 3 ቢሊየን ዶላር ለማሳደግ ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት ተግባራዊ እየተደረገ የሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለቡና ዘርፉ ዕድገት ትልቅ ድርሻ ማበርከቱንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በዓለም ላይ ካለው የዓረቢካ ቡና ዝርያ 90 በመቶ የሚሆነውን የጄኔቲክ ብዝሃ-ህይወት በመያዟ ለዓለም የቡና ኢንዱስትሪ እንደ የዘር ባንክ እንደምትቆጠርም ተናግረዋል፡፡ ይህም ለተለዋዋጭ የአየር ንብረት የማይበገሩ ዝርያዎችን ለማምረት ልዩ ዕድል መፍጠሩን ነው የተናገሩት፡፡ ጥሬ ቡናን ከመላክ ባለፈ እሴት የተጨመረበት ቡናን ወደ ውጪ ለመላክ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ በአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና(AfCFTA) አማካኝነት በአህጉሪቱ ውስጥ የቡና ንግድን ለማጠናከር የፖሊሲ ማሻሻያዎች እየተደረጉ መሆናቸውንም እንዲሁ፡፡ ኮንፍረንሱ የአፍሪካ ቡና አምራቾችን ከዓለም አቀፍ ገዢዎች ጋር በቀጥታ እንዲገናኙ የማድረግ ብሎም የንግድ ሰንሰለቱን ፍትሐዊ ለማድረግ እንደሚረዳም ነው የጠቆሙት፡፡ የቡናና ሻይ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሻፊ ሁመር እንደገለጹት፤ መንግስት በቡናው ዘርፍ የጀመረው የሪፎርም ስራ አስደናቂ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል ብለዋል። ይህ የለውጥ እርምጃ ከአምራች አርሶ አደሩ ጀምሮ በንግድ ሰንሰለቱ ውስጥ ያሉ አካላትን ተጠቃሚነት በእጅጉ ማሳደጉን ገልጸዋል። የዘርፉን የኢኮኖሚ አቅም ይበልጥ ለማጠናከር ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራ ጠቅሰው፤ አሁን እየተካሄደ የሚገኘው ጉባኤ አፍሪካ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት ተጠቅማ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን የቡና ገበያ ድርሻ እንድታሳድግ መልካም አጋጣሚ እንደሚፈጥርም አስገንዝበዋል።
የሴፍቲኔት ፕሮግራም የሥራ ባህላችንን ለማሳደግ አግዞናል- በኮምቦልቻ ከተማ የፕሮግራሙ ተጠቃሚዎች
Feb 5, 2026 58
ኮምቦልቻ ፤ጥር 28/2018 (ኢዜአ)፡- የከተማ ሴፍቲኔት ፕሮግራም ጥሪት ለማፍራትና የሥራ ባህላቸውን ለማሳደግ እንዳገዛቸው በኮምቦልቻ ከተማ የፕሮግራሙ ተጠቃሚዎች ገለፁ። በኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር በከተማ ሴፍቲኔት ታቅፈው ህይወታቸውን የለወጡ 1 ሺህ 268 ተጠቃሚዎች ዛሬ ተመርቀዋል። ከፕሮግራሙ ተመራቂዎች መካከል አቶ ዳንኤል አሊ ለኢዜአ እንደገለጹት የሚሰራ ጉልበትና የስራ ፍላጎት ቢኖራቸውም በገንዘብ እጥረት በችግር ውስጥ መቆየታቸውን አስታውስዋል። ይህን ችግር ለመቅረፍም በሴፍቲኔት መርሃ ግብር አረንጓዴ ልማት ተሰማርተው ገቢ ከማግኘታቸው ባሻገር በአትክልት ልማት ተሰማርተው አኗኗራቸው እንዲለወጡ እንዳገዛቸው ገልጸዋል። ከአትክልት ልማቱ ካገኙት ገቢም ቤተሰባቸውን ከማስተዳደር አልፈው ወደ ፍየል እርባታ ስራ ለመሸጋገር ማቀዳቸውን አስረድተዋል። ሌላዋ የፕሮግራሙ ተጠቃሚ ወይዘሮ ትግስት ጫኔ በበኩላቸው በፕሮግራሙ የከተማውን ውበትና ልማት ከመጠበቅ ባለፈ በተመቻቸላቸው የገቢ ማስገኛ ሥራ ሀብት ማፍራት መጀመራቸውን ተናግረዋል። በከተማው የቆሻሻ መጣያ የነበሩ አካባቢዎችን በማጽዳት ድንች፣ ሽንኩርትና ሌሎች አትክልቶችን በማልማት በሚያገኙት ገቢ ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መሆኑን ገልጸዋል። በተጨማሪም ከሚያገኙት ገቢ በመቆጠብና ባገኙት ድጋፍ በመታገዝ በእንጀራ መጋገር ሥራ ተሰማርተው ለምግብ ቤቶችና ለሌሎችም እያስረከቡ የተሻለ ገቢ ማግኘት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። በፕሮግራሙ ታቅፈው በተመቻቸላቸው የመስሪያ ቦታና የሥራ እድል ከችግርና ከተረጂነት ተላቀው እራሳቸውን መቻላቸውን የገለጹት ደግሞ ሌላው ተጠቃሚ አቶ ማዘንጊያ በለጠ ናቸው። የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር የምግብ ዋስትናና ሴፍቲኔት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ እታፈራሁ አሰግደው እንደገለጹት ባለፉት ሶስት ዓመታት በፕሮግራሙ የታቀፉ 1 ሺህ 268 የቤተሰብ መሪዎች ዛሬ ተመርቀዋል። በከተማ ግብርና፣ በአገልግሎት፣ በግንባታና ሌሎች ልማቶች በመሰማራት ምርታማነታቸውን በማሳደግና ከተረጂነት በመውጣት ጥሪት ማፍራት መቻላቻውን አስገንዝበዋል። የሥራ ተነሳሽነታቸውን በማሳደግና የቁጠባ ባህላቸውን በማሳደግ ከራሳቸው ተርፈው ሌሎችን በመደገፍ ምሳሌ መሆን መቻላቸውንም ገልጸዋል። የከተማው ከንቲባ አቶ መሀመድአሚን የሱፍ በበኩላቸው፤ ዛሬ ከፕሮግራሙ ለሚመረቁ ዜጎች የመስሪያ ቦታና የገንዘብ ድጋፍ በማድረግ ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ይሰራል ብለዋል። በምረቃ መድረኩ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ከተማና መሰረት ልማት ቢሮ ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) እንዳሉት በክልሉ በርካታ ዜጎችን በምግብ ዋስትናና ሴፍቲኔት ፕሮግራም በማቀፍ ከድህነት እንዲወጡ ተደርጓል። በከተማ ግብርና፣ በእንሰሳት እርባታና ማድለብ፣ በሌማት ትሩፋትና ሌሎች የሥራ ዘርፎች ተሰማርተው ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ በማድረግም ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል። በምረቃ ፕሮግራሙ የክልልና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች፣ የሐይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በኩታ ገጠም ኮረሪማን በማልማት የመሎኮዛ ወረዳ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ሆነዋል
Feb 5, 2026 65
ሳውላ ፤ጥር 28/2018 (ኢዜአ) ፡-በኩታ ገጠም ኮረሪማን በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን በጎፋ ዞን የመሎኮዛ ወረዳ አርሶ አደሮች ተናገሩ። ከደጋ እስከ ቆላ አየር ንብረት የያዘው የጎፋ ዞን ቡና፣ ቅመማ ቅመም፣ ፍራፍሬና የተለያዩ ሰብሎችን ለማምረት የሚያስችል ዕምቅ ሀብት የያዘ ሲሆን በተለይ በደጋማ አካባቢዎች በስፋት ኮረሪማ ይመረትበታል። በዞኑ ኮረሪማ አምራች ከሆኑት ወረዳዎች ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዘው የመሎኮዛ ወረዳ ከ15 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኮረሪማ ተሸፍኗል። በወረዳው ኮረሪማ ከሚያመርቱ አርሶ አደሮች መካከል ሞዴል አርሶ አደር ደነቀ ጎሹ አንዱ ናቸው፤ አርሶ አደሩ በኮረሪማና ቅመማ ቅመም ካለሙት አምስት ሄክታር መሬት 30 ኩንታል ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። ኮረሪማን በኩታ ገጠም የእረሻ ስነ-ዘዴ በማከናወናቸው ምርታማነታቸውን ማደጉን ተናግረዋል። በዚህም አንድ ኩንታል ኮረሪማን ከ150 ሺህ እስከ 200 ሺህ ብር በመሸጥ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው መላቁንም አክለዋል። በዚህም ዘመናዊ የመኖሪያ ቤት ከመገንባት ባለፈ ተጨማሪ ገቢ የሚያመነጭ ወፍጮ በመትከል እየሰሩ መሆኑን ነው የጠቀሱት። ምርታማነቱ የተሻሻለ የኮረሪማ ቅመም በ2 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ላይ በኩታ ገጠም በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ ሌላው አርሶ አደር አርሼ ዘለቀ ናቸው። ከልማቱም በዓመት እስከ 30 ኩንታል ምርት እያገኙ መሆኑን ተናግረው በኩንታል ከ150 ሺህ ብር በላይ በመሸጥ ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የተናገሩት። የመሎኮዛ ወረዳ ቡናና ቅመማ ቅመም ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አማረ አገኘሁ እንዳሉት በወረዳው በኮረሪማ ልማት ከተሸፈነው 15 ሺህ 520 ሄክታር መሬት ውስጥ 1 ሺህ 700 ሄክታሩ በኩታ ገጠም የለማ ነው። በወረዳው ከለማው ኮረሪማ በዓመት 116 ሺህ ኩንታል እንደሚሰበሰብ ገልጸው ውጤታማነቱን ለማሳደግም ለአርሶ አደሩ የተሻሻሉ ዝርያዎችን ከማቅረብ ባለፈ ድጋፍና ክትትል መደረጉን አንስተዋል። በጎፋ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊና የቡናና ቅመማ ቅመም ዘርፍ ኃላፊ አቶ ኑርአዲስ አደም እንዳሉት በዞኑ መሎኮዛ፣ ገዜ ጎፋና ሌሎች ደጋማ አካባቢዎች ኮረሪማ በስፋት ይመረታል። አርሶ አደሩ ምርቱን በስፋት ማምረት እንዲችል በባለሙያ ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝና ከጊዜ ወደ ጊዜ የማሳ ሽፋኑ እያደገ እንደመጣ ጠቁመዋል። በገበያ ያለው ዋጋ እያደገ መምጣቱ ለዚህ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የተናገሩት አቶ ኑርአዲስ ከዞኑ በተያዘው ዓመት ከ30 ሺህ ቶን በላይ ምርት ለማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ እቅድ ተይዞ እስካሁን ከ8 ሺህ ቶን በላይ ለገበያ መቅረቡን ገልጸዋል።
በግማሽ ዓመቱ 63 አዳዲስ የገጠር ቀበሌዎች የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ሆነዋል
Feb 5, 2026 48
አዲስ አበባ፤ ጥር 28/2018(ኢዜአ)፦ በግማሽ ዓመቱ 63 አዳዲስ የገጠር ቀበሌዎችና መንደሮችን የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ማድረጉን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስታወቀ፡፡ የአገልግሎቱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው የስድስት ወራት አፈጻጸምን በተመለከተ በሰጡት መግለጫ በዘርፉ በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን አብራርተዋል። በግማሽ ዓመቱ አዳዲስ ደንበኞችን ተጠቃሚ ከማድረግ በኩል ከዕቅድ በላይ አፈጻጸም መመዝገቡን ጠቅሰው፤ 63 የገጠር ቀበሌዎችና መንደሮች ወደ ኃይል መስመር መግባታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የገጠር ቀበሌዎቹን ተጠቃሚ ማድረግ የተቻለው ከዋናው መስመርና ከፀሐይ ኃይል መሆኑንም ጨምረው ጠቁመዋል፡፡ ይህም የገጠሩን ማህበረሰብ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትልቅ ሚና እንደሚኖረው ገልጸዋል። ይህንን አፈጻጸም ተከትሎ በሀገር አቀፍ ደረጃ የኤሌክትሪክ አገልግሎት የሚያገኙ ደንበኞች ቁጥር እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ስድስት ወራት ከተለያዩ የገቢ አማራጮች 52 ነጥብ 26 ቢሊየን ብር መሰብሰብ መቻሉንም ተናግረዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ የተለወጠ የስራ ባህል የከተማዋን ኢኮኖሚ 24 ሰዓት እያንቀሳቀሰ ይገኛል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Feb 5, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ጥር 28/2018(ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ የተለወጠ የስራ ባህል የከተማዋን ኢኮኖሚ 24 ሰዓት እያንቀሳቀሰ እና በርካታ የስራ እድሎችም እየፈጠረ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናገሩ ከንቲባ አዳነች በካዛንችስ አካባቢ የሚገነባውን የህጻናት አለም ፓርክ እና በቦሌ መድኃኔዓለም እና 22 አካባቢ የሚገነቡ የኮሪደር ልማት አገናኝ መስመሮችን የምሽት የስራ እንቅስቃሴ ገምግመዋል። አዲስ አበባ ከተማን ውብ ጽዱ እና ለኑሮ ምቹ ለማድረግ የሚከናወነው ተግባር በፍጥነት እየተፈጸመ ነዋሪውም ውጤቱን በተጨባጭ እየተመለከተ ይገኛል። ይህ የሆነው ደግሞ በከተማዋ በተለወጠው 24/7 የመስራት የስራ ባህል እና ያልተቋረጠ የአመራር ክትትል ስራው በፍጥነት እየተከናወነ በመሆኑ ነው። በካዛንችስ አካባቢ እየተገነባ የሚገኘውን የህጻናት አለም ፓርክ ፣ በቦሌ መድኃኔዓለም እና 22 አካባቢ የሚገነቡ የኮሪደር ልማት አገናኝ መስመሮችን የምሽት የስራ እንቅስቃሴ ተዘዋውረው የጎበኙት ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከተማዋን የማልማቱ ተግባር የነገ ትውልድንም ታሳቢ ባደረገ መልኩ የሚካሄድ በመሆኑ የህጻናት አለም ፓርክ አለም አቀፍ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ እየተገነባ መሆኑን ገልጸዋል። የፓርኩ ግንባታ ስራ በኢትዮጵያውያን ትጋት 24/7 እየተካሄደ መሆኑን የገለጹት ከንቲባዋ ለግንባታው የሚውለው አብዛኛው ግብዓትም የሀገር ውስጥ መሆኑንና ለበርካቶችም የስራ እድል መፈጠሩን ተናግረዋል። በቦሌ መድኃኔዓለም እና በ22 አካባቢ የሚገነቡ የኮሪደር ልማት አገናኝ መስመሮች ግንባታም በተለመደው የግንባታ ፍጥነት እየተካሄደ መሆኑን የሚናገሩት ከንቲባዋ የግል ዘርፉም በተለወጠው የስራ ባህል ለልማቱ አጋዥ እየሆነ ነው ብለዋል። ይህ የከተማዋ የተለወጠ 24/7 የመስራት የስራ ባህል የከተማዋን ኢኮኖሚ 24 ሰዓት እያንቀሳቀሰ እና በርካታ የስራ እድሎችንም እየፈጠረ መሆኑን ነው ከንቲባ አዳነች አቤቤ የተናገሩት። አዲስ አበባ ከተማን ለኑሮ ምቹ እና አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ብሎም መጪው ትውልድ ያደገች እና የበለጸገች ሆና የሚረካባት ለማድረግ የሚከናወነው ይህ ተግባር በተያዘው አግባብ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው ከንቲባ አዳነች አቤቤ የገለጹት።
በምስራቅ አፍሪካ የባህር ጠረፍ የኢትዮጵያ ተጠቃሚ አለመሆን ፍትሕዊነት የጎደለው ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Feb 5, 2026 70
አዲስ አበባ፤ ጥር 28/2018(ኢዜአ)፡- በምስራቅ አፍሪካ ቀጣና የባህር ጠረፍ በቅርብ ርቀት ላይ የምትገኘው ኢትዮጵያ ተጠቃሚ አለመሆኗ ፍትሃዊነት የጎደለው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ስድስተኛው የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት አምስተኛ ዓመት የሥራ ዘመን 10ኛ መደበኛ ስብሰባውን አካሂዷል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በፌዴራል መንግሥት የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት የሥራ አፈፃጸም ሪፖርት ላይ ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም በተመለከቱ ጉዳዮችን አስመልክተው በሰጡት ማብራሪያ፣ ኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤት የመሆን ጥያቄዋ የጋራ ብልፅግና መርህን የተከተለ ነው ብለዋል። የምስራቅ አፍሪካ ከምፅዋ እስከ ሞቃዲሾ ያለው የቀይ ባህር ቀጣና አምስት ሺህ ኪሎ ሜትር የባህር ጠረፍ እንደሚሸፍን ገልጸው በዚህ ለሁሉም በሚበቃ ሰፊ የባህር ዳርቻ ከ130 ሚሊየን በላይ ህዝብ ያላት ኢትዮጵያ ምንም ዓይነት ተጠቃሚ አለመሆኗ ፍትሕዊነት የጎደለው ነው ብለዋል። ይህ ጥያቄ ፍትዊ ካልሆነ ዓለም ላይ ፍትሕ የለም ማለት ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ኢትዮጵያ የባህር በር ካላገኘች ለጎረቤት ሀገራትም ጭምር የኢኮኖሚ ዕዳ እንደምትሆን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄዋን በኃይል ሳይሆን በሰላማዊ መንገድና በሕግ አግባብ ለመፍታት ቁርጠኛ መሆኗንም አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት በሊዝ ስምምነት የወደብ አገልግሎት ባለቤት መሆን እንደሚቻልም አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ በቀጣናው ትልቅ የገበያና የኢኮኖሚ አቅም በመሆኗ ጎረቤት ሀገራት ከኢትዮጵያ ጋር ተደጋግፈው ማደግ እንጂ ኢትዮጵያን ከተፈጥሮ ፀጋዋ በማራቅ ትርፋማ መሆን እንደማይችሉ ገልጸዋል።
የሻኪሶ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ሥራ በይፋ ተጀመረ
Feb 5, 2026 88
ሻኪሶ፤ ጥር 28/2018 (ኢዜአ) ፡-የሻኪሶ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ሥራ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ በተገኙበት ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። የሻኪሶ አውሮፕላን ማረፊያ በ124 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ላይ የሚገነባ መሆኑ ተጠቁሟል። በይፋዊ የሥራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድርን ጨምሮ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው፣ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አህመድ፣ እንዲሁም ሌሎች የፌዴራል፣ የክልልና የጉጂ ዞን አመራሮችና አባ ገዳዎች ተገኝተዋል።
በአማራ ክልል የሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያጎለብቱ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Feb 4, 2026 66
ባህርዳር ፤ጥር 27/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያጎለብቱ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ሴቶች፣ ወጣቶችና ማሕበራዊ ጉዳይ ቢሮ አስታወቀ። ሴቶችን በኢኮኖሚ ማብቃት ላይ ያተኮረ ክልላዊ ፎረም ዛሬ በባህርዳር ተመስርቷል ። የአማራ ክልል ሴቶች፣ ወጣቶችና ማሕበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊና የፎረሙ ሰብሳቢ ብርቱካን ሲሳይ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፣በክልሉ የሴቶችን አቅም ለማጎልበትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። የፎረሙ ዋና ዓላማ የሴቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ተቋማት ቅንጅታዊ አሰራራቸውን አንዲያጠናክሩ ማድረግ መሆኑን ገልጸዋል። ሴቶች በልማትና በመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ላይ ንቁ ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ የፎረሙ መመስረት የጎላ ጠቀሜታ እንደሚኖረው አመልክተዋል። የፎረሙ አባል ተቋማት በመደበኛ ስራዎቻቸው የሴቶችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ተግባራት ላይ ትኩረት ሰጥተው መስራትና ተጨባጭ ውጤት ማምጣት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ሴቶች ወደ ስራ ለመግባት በሚያደርጉት ጥረት የሚያጋጥማቸውን የፋይናንስ ችግር ለመፍታት የፋይናንስ ምንጭን ማስፋት ላይ የተቋማት ርብርብ ወሳኝ መሆኑን አመልክተዋል። የክልሉ ሥራና ሥልጠና ቢሮ ኃላፊና የፎረሙ ምክትል ሰብሳቢ ስቡህ ገበያው (ዶ/ር) በበኩላቸው ሴቶችን በሚፈልጉት ሙያ በማሰልጠን፣ በማደራጀትና ወደ ስራ በማስገባት ረገድ በሚደረገው ጥረት የመሬትና የብድር አቅርቦት እጥረት ዋነኛ ችግር መሆኑን አንስተዋል። የፎረሙ መመስረት እንደዚህ አይነት ችግሮችን በተቀናጀ አግባብ በመፍታት የሴቶችን ዘላቂ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥም ያስችላል ብለዋል። የፎረሙ መቋቋም ሴቶች በግብርናው ዘርፍ ተሰማርተው ዘላቂ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን የሚያረጋግጡበት ዕድል ይፈጥራል ያሉት ደግሞ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊና የፎረሙ አባል ደረጀ ማንደፍሮ ናቸው። የአማራ ክልል መሬት ቢሮ ኃላፊ ሲሳይ ዳምጤ በበኩላቸው፣ሴቶችን የገጠር መሬት ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፣ፎረሙ ተግባሩን የበለጠ ለማጠናከር ያግዛል ብለዋል። በፎረሙ መመስረቻ መድረክ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት እንዲሁም ከክልል እስከ ዞን የሚገኙ ሴት አደረጃጀቶች ተሳትፈዋል።
በኢትዮጵያ እየታየ ያለውን ሁለንተናዊ ልማትና ዕድገት ለማስቀጠል የድርሻችንን እንወጣለን
Feb 4, 2026 63
ወልዲያ ፤ ጥር 27/2018(ኢዜአ)፡-በኢትዮጵያ እየታየ ያለውን ሁለንተናዊ ልማትና ዕድገት ለማስቀጠል የድርሻቸውን እንደሚወጡ የወልዲያ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ትናንት ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የመንግስትን የ2018 በጀት ስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም በተመለከተ ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በዚህም መንግስታቸው፣ ባለፉት ስድስት ወራት በማሕበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ጉዳዮች ያከናወናቸው ተግባራትና የተገኙ ውጤቶችን አብራርተዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩን ማብራሪያ አስመልክቶ ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የወልዲያ ከተማ ነዋሪዎች መንግስት በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የህዝብን የሰላምና ልማት ጥያዌዎች ለመመለስ ያከናወናቸውን ተግባራት አድንቀዋል። ይህንንም በኢትዮጵያ እየታየ ያለውን ሁለንተናዊ ልማትና ዕድገት ለማስቀጠልም የድርሻቸውን እንደሚወጡ ነዋሪዎቹ አረጋግጠዋል። አስተያየታቸወን ከሰጡ የወልዲያ ነዋሪዎቸ መካከል ይድነቃቸው ለገሰ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ቁርጠኛ አመራር በኢትዮጵያ የሚታይ ዕድገት መምጣቱን ገልጸዋል። በኮሪደር ልማት፣ በበጋ መስኖ ስንዴ፣ በሌማት ትሩፋትና በሌሎችም የልማት መስኮች እየታየ ያለው ውጤት ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን አመልክተዋል። በኢንዱስትሪና በማዕድን ዘርፉ እየታየ ያለው ዕድገት ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል እየፈጠረ ነው ብለዋል። እንደ ሀገርም ሆነ በክልል ደረጃ የተጀመሩ የልማትና የሰላም ግንባታ ሥራዎች የበለጠ እንዲጠናከሩ የድርሻቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። መንግስት የጀመራቸው ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የኢትዮጰያን መጻዒ ዕጣ ፈንታ የተሻለ ለማድረግ ቁልፍ ሚና አንዳላቸው የተናገሩት ደግሞ በላይ ገላው ናቸው። ቀደም ሲል ትኩረት ተነፍጎት የቆየው የቱሪዝም ዘርፍን ጨምሮ በግብርና ምርትና ምርታማነት ላይ እየታየ ያለው ለውጥ የመንግስትን ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል። አሁን በኢትዮጵያ እየታየ ያለውን ሁለንተናዊ ልማት ለማስቀጠል ሁሉም ዜጋ ለሀገሩ ሰላምና ልማት ዘብ ሊቆም አንደሚገባ አመልክተዋል። መንግስት ዲጂታል ኢትዮጵያን በመገንባት የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አያደረገ ያለውን ጥረት ያደነቀው ደግሞ ወጣት አበበ አለማየሁ ነው። ወጣቶች የዲጂታል ክህሎታቸውን በማሳደግ በሀገር ወስጥና በውጭ ሀገራት የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸው ለዚህ ማሳያ መሆኑን ጠቅሷል። ወጣቶች በየአካበቢያቸው የሚፈጠሩ ጥቃቅን ቸግሮችን በሰለጠነ መንገድ በመፍታት ለአገራቸው የልማትና የቴክኖሎጂ ዕድገት የድርሻቸውን በመወጣት ከመንግስት ጎን መቆም ይገባል ብሏል።
በምስራቅ ቦረና ዞን በዘንድሮው ዓመት ከ178 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበልግ ይለማል
Feb 4, 2026 78
ነገሌ ቦረና፤ ጥር 27/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ቦረና ዞን በዘንድሮ የበልግ አዝመራ ከ178 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት መታቀዱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በኦሮሚያ ክልል ዝናብ አጠር ዞኖች ከሆኑት አንዱ የምስራቅ ቦረና ዞን ነው። ዞኑ አርብቶ አደር ማህበረሰብ የሚበዛው ቢሆንም የክልሉ መንግስት የተለያዩ ኢንሼቲቮችን ቀርጾ ማሕበረሰቡ ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን በሌሎች የእርሻ ልማት በመሳተፍ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ እያደረገ ነው። በተለይም አካባቢው የበልግ አብቃይ እንደመሆኑ ያሉትን የውሃ አማራጮች በመጠቀም ምርትና ምርታማቱን ለማሳደግ ያላሰለሰ ጥረት እያደረገ ይገኛል። በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ ቦነያ ሁቃ ለኢዜአ እንዳስታወቁት ፤በዞኑ በአብዛኛው ቆላማ ወረዳዎች የዝናብ እጥረት በማጋጠሙ ባለፈው የመኸር ወቅት የሚጠበቀው ምርት ለማግኝት አልተቻለም። ይህንን ለማካካስ በዘንድሮው የበልግ ወቅት 178 ሺህ 713 ሄክታር መሬት ለማልማት ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል። በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴ 48 ሺህ 773 ሄክታር መሬት ታርሶ ለዘር መዘጋጀቱን አስታውቀዋል፡፡ ዞኑ ከበልግ ወቅት የእርሻ ስራ 3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ማቀዱን አስታውቀዋል። በአሁኑ ወቅት የማሳ ዝግጅት ስራውን የሚያሳልጡ በርካታ ትራክተሮች ወደ ዞኑ የገቡ ሲሆን፤ ከ78 ሺህ በላይ ከፊል አርብቶ አደሮችም በዚሁ ስራ ላይ በመሳተፍ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። በልማቱ ከተሳተፉት ከፊል አርሶ አደሮች መካከል በዞኑ ሊበን ወረዳ የጎቢቻ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አብዲኑር መሀመድ እንዳሉት፤ በበልግ አዝመራው የተሻለ ምርት ለማግኘት እንዲቻል የማሳ ዝግጅት ላይ በትኩረት እየተሰራ ነው። ባለፈው መኸር የምርት እጥረት አጋጥሞ የነበረ ቢሆንም በዘንድሮው አመት የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እየተጉ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡ በሊበን ወረዳ የሲሚንቶ ቀበሌ ነዋሪ ወጣት ሁሴን አብዱላሂ በበኩሉ በበልግ አዝመራው ስንዴና ጤፍ ለማልማት የማሳ ዝግጅት መጀመሩን ይናገራል። የሊበን ወረዳ ቆላና ዝናብ አጠር ቢሆንም በበልጉ አዝመራ የተሻሻለ የግብርና አሰራርና የውሃ አማራጮችን በመጠቀም ጥሩ ምርት የመሰብሰብ ልምድ እንዳለው ነው የሚገልፀው።
በክልሉ ባለፉት ስድስት ወራት ውጤታማ የልማትና መልካም አስተዳደር ሥራዎች ተከናውነዋል
Feb 4, 2026 66
ሐዋሳ፤ ጥር 27/2018 (ኢዜአ) :- በሲዳማ ክልል በ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያው ስድስት ወራት ውጤታማ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች መከናወናቸውን የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አብርሀም ማርሻሎ አስታወቁ። በክልሉ የመንግስትና የፓርቲ የግማሽ በጀት አመት አፈጻጸም ግምገማና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በሐዋሳ እየተካሄደ ነው። የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አብርሀም ማርሻሎ መድረኩን አስመልክቶ ለጋዜጠኞች ማብራሪያ ሰጥተዋል። በዚሁ ጊዜ በክልሉ ባለፉት ስድስት ወራት የሕዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል። ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም አርሶ-አደሩን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም አንስተዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር የተሻሻለ ዝርያ ያላቸውን የዶሮና የወተት ላሞችን በማቅረብና በማዳቀል አርሶ አደሩ ተገቢውን ጥቅም ማግኘት እንዲችል መደረጉን ጠቁመዋል። የመሰረተ ልማት ጥያቄዎችን በተቀናጀ መንገድ ለመፍታት ጥረት መደረጉን ጠቅሰው፣ በመንገድ፣ በመጠጥ ውሃ አቅርቦትና በሌሎችም አበረታች ውጤት መገኘቱን አመልክተዋል። በክልሉ በሁሉም ከተሞችና በገጠር እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር ልማት ስራዎች ለስራ፣ ለኑሮና ለመዝናኛ ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውንም ነው ያብራሩት። ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የሚነሱ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎትን ከሐዋሳ በተጨማሪ በሌሎች ከተሞች ለማስጀመር ቅድመ ዝግጅት መደረጉንም አመልክተዋል። ጠቅላላ ምርጫው ሰላማዊ፣ ፈትሃዊና ነጻ እንዲሆንም እየተሰራ ነው ብለዋል። ዛሬን ጨምሮ ለቀጣዮቹ ሶስት ቀናት በሚካሄደው የግምገማ መድረክ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድርን ጨምሮ የካቢኔ አባላት፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች እንዲሁም የፓርቲ ጽህፈት ቤት አመራሮች እየተሳተፉ ነው።
የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርም ለግሉ ዘርፍ ምቹ መደላድል ፈጥሯል
Feb 4, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ጥር 27/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርም ለግሉ ዘርፍ ምቹ መደላድል መፍጠሩን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። 15ኛው የኢትዮ-ቻምበር ዓለም አቀፍ የንግድ ትርኢት "የኢትዮጵያን ይግዙ፤ በኢትዮጵያ ኢንቨስት ያድርጉ" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ መካሄድ ጀምሯል። በርካታ የሀገር ውስጥና የውጭ ኩባንያዎች የሚሳተፉበት ይህ የንግድ ትርኢት ከዛሬ ጥር 27 እስከ የካቲት 1 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ሰብስብ አባፊራ እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በመክፈቻ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ተገኝተዋል። ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ በማሳደግ ረገድ ምቹ መደላድል መፍጠሩን ገልጸዋል። በዚህም ኢትዮጵያን የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ በሚከናውኑ ተግባራት የግሉ ዘርፍ የኢኮኖሚ ድርሻ በከፍተኛ ፍጥነት ዕድገት እያስመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮ-ቻምበር ዓለም አቀፍ የንግድ ትርኢት የሀገር ውስጥ ምርቶችን በዓለም አቀፍ ደረጃ በማስተዋወቅ የገበያና የንግድ ትስስርን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውም ጠቁመዋል። በቀጣይም የግሉ ዘርፍ በንግድና ኢንቨስትመንት ያለውን ተሳትፎ ለማሻሻል የሚደረጉ የድጋፍና ክትትል ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ሰብስብ አባፊራ በበኩላቸው፤ የሀገሪቷን ብልጽግና ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም ምክር ቤቱ የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚ ዕድገቱ ላይ የጎላ ተሳትፎ እንዲኖረው የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን ጠቁመዋል። ኤግዚቢሽኑ የኢትዮጵያ ምርቶች በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ከማድረጉም ባለፈ፣ የሀገሪቱን የንግድ እንቅስቃሴ በማነቃቃትና አዳዲስ የውጭ ኢንቨስትመንቶችን በመሳብ ረገድ ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል። የምክር ቤቱ ዋና ጸሐፊ ቀነኒሳ ለሚ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በንግድ ትርኢቱ ላይ ከ300 በላይ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ድርጅቶች መሳተፋቸውን ገልጸዋል። ከእነዚህም መካከል ከ20 በላይ ከሚሆኑ ሀገራት የመጡ 50 ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ይገኙበታል። ዝግጅቱ ምርትን ከማስተዋወቅ ባለፈ በተቋማት መካከል የልምድ ልውውጥና የቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲሳለጥ ምቹ አጋጣሚ እንደሚፈጥርም ተናግረዋል።
የዕዳ ጫናን ለመቀነስ እየተወሰዱ ያሉ የመፍትሄ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ ነው
Feb 4, 2026 107
አዲስ አበባ፤ ጥር 27/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያን የዕዳ ጫና ለመቀነስ እየተወሰዱ ያሉ የመፍትሄ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገለጹ። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የህክምና መሳሪያዎች አቅርቦት ፕሮጀክት ለምዕራፍ ሁለት ማስፈጸሚያ የሚውል የብድር ስምምነት ለማጽደቅ የቀረበ ረቂቅ አዋጅ ላይ አስረጂ የውይይት መድረክ አካሂዷል። በውይይት መድረኩ የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አሕመድ ሽዴ የብድር ሥምምነቱን አስመልክቶ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸው የብድር ሥምምነቱ ለጤና ተቋማት የህክምና ቁሳቁስ በማሟላትና ባለሙያዎችን በማሰልጠን ህብረተሰቡን የጤና አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ ያለመ ነው ብለዋል። ለዚህም 30 ሚሊዮን ዶላር ኮንሴሽናል ብድር ከደቡብ ኮሪያ ኢምፖርት ኤክስፖርት ባንክ የሚገኝ መሆኑን ጠቅሰው፥ ብድሩ በ40 ዓመታት ውስጥ ተከፍሎ የሚጠናቀቅ 0 ነጥብ 01 በመቶ ወለድ ያለው መሆኑን አብራርተዋል። እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ የዕዳ ጫናን ለመቀነስ ተግባራዊ የተደረጉ የመፍትሄ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ ነው። ባለፉት የለውጥ ዓመታት እንደ ሀገር ምንም ዓይነት የኮሜርሺያል ብድር አልወሰድንም ያሉት ሚኒስትሩ፤ ከአበዳሪ ሀገራት ጋር በመደራደር የዕዳ ሽግሽግ እንዲደረግ ርብርቡ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። ጥቅል ሀገራዊ ምርትና የወጪ ንግድ እያደገ መምጣቱን ገልጸው ፤ ይህም የዕዳ ጫናን መቀነስን ጨምሮ ጤናማ የፋይናንስ ስትራቴጂ ተግባራዊ በመደረጉ የመጣ ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። የህክምና መሳሪያዎች አቅርቦት ፕሮጀክት ምዕራፍ ሁለት ማስፈጸሚያ የሚውል የብድር ስምምነትም በረጅም ጊዜ የሚመለስ እና ዝቅተኛ ወለድ ያለው መሆኑ ከአጠቃላይ የብድር ስትራቴጂ አኳያ ተፈላጊ ነው ብለዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ደሳለኝ ወዳጄ በበኩላቸው፤ የዕዳ ጫናን ለመቀነስ እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎች የሚበረታቱ መሆናቸውንም ጠቁመዋል። የህክምና መሳሪያዎች አቅርቦት ፕሮጀክት ምዕራፍ ሁለት ማስፈጸሚያ የሚውለው የብድር ስምምነት፥ የጤና ተቋማትን የህክምና ግበዓት እጥረት ለመፍታት አዎንታዊ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። አዋጁ ጸድቆ ሥራ ላይ እንዲውል ቋሚ ኮሚቴው አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል።
የፋይናንስ ዘርፉን ለማዘመን የተተገበሩ ሪፎርሞች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው
Feb 4, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ጥር 27/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያን የፋይናንስ ዘርፍ ለማዘመንና ኢኮኖሚውን ለማነቃቃት እየተተገበሩ የሚገኙ የሪፎርም እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 10ኛ መደበኛ ስብሰባ ተገኝተው በመንግሥት የ6 ወራት የእቅድ አፈፃፀም ሪፖርት ላይ ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። የኢትዮጵያን የፋይናንስ ዘርፍ ለማዘመንና ኢኮኖሚውን ለማነቃቃት መጠነ ሰፊ ሪፎርም በመተግበር ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በባንኮች እርስ በእርሳቸው የገንዘብና የዶላር ግብይት እንዲፈጽሙ በማድረግ፥ ባለፈው ስድስት ወር ከግማሽ ትሪሊየን ብር ያላነሰ ገንዘብ እርስ በእርስ መገበያየታቸውን ገልጸዋል። ይህም ትልቅ የገንዘብ ምንጭ ማስፊያ መንገድ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በዚህ ምክንያት በስድስት ወራት የገንዝብ አቅርቦቱ ከ10 በመቶ በላይ ቁጠባ ደግሞ ከ44 በመቶ በላይ ማደጉን ነው የተናገሩት፡፡ የተሰበሰበ ብድርም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር 68 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን ጠቅሰው አዲስ የቀረበው የብድር መጠንም በ123 በመቶ ማደጉን አብራርተዋል፡፡ አጠቃላይ የቀረበው ብድር ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር 123 በመቶ የጨመረ ሲሆን፥ ከቀረበው ውስጥ 90 በመቶው ለግሉ ዘርፍ የተሰጠ መሆኑን ገልጸው በዘርፉ ትልቅ እመርታ እየመጣ ለመሆኑ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የፋይናንስ ዘርፉ ለውጭ ባንኮች መከፈቱ ካፒታል እና ቴክኖሎጂ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጣ ዕድል የሚፈጥር መሆኑን በማንሳት፥ ለዘርፉና ለአጠቃላይ ሀገራዊ ዕድገት ትልቅ ሚና እንደሚኖረውም ነው ያስረዱት። የሀገር ውስጥ ባንኮች ለኢኮኖሚው ያላቸው ድርሻ ከ5 እስከ 7 በመቶ ብቻ መሆኑን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ውድድርን ለመፍጠርና ቴክኖሎጂን ለማስፋፋት የውጭ ባንኮች መግባት አስፈላጊ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል። በዚህ ሂደት የሀገር ውስጥ ባንኮችን ጥቅም ለመጠበቅ የባለቤትነት ድርሻ ገደብ መቀመጡን ገልጸው፤ በአጠቃላይ በዘርፉ የውጭ ባለሀብቶች ድርሻ ከ49 በመቶ እንደማይበልጥ አስረድተዋል። ይህ ሪፎርም የሀገሪቱን የፋይናንስ አቅም በማጠናከር ለዜጎችና ለንግዱ ማህበረሰብ የተሻለ ዕድል እንደሚፈጥር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው አመላክተዋል።
የመደመር መንግሥት የሀገሪቱን የዕዳ ጫና በመቀነስ ረገድ ከፍተኛ ውጤት አስመዝግቧል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Feb 4, 2026 85
አዲስ አበባ፤ ጥር 27/2018 (ኢዜአ)፡- የመደመር መንግሥት የሀገሪቱን የዕዳ ጫና በመቀነስ ረገድ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገቡን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 10ኛ መደበኛ ስብሰባ ተገኝተው በመንግሥት የ6 ወራት የእቅድ አፈፃፀም ሪፖርት ላይ ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም የለውጡ መንግሥት በዕዳ ቅነሳና አስተዳደር ሥራ ሊመሰገን የሚገባው ሥራ መሥራቱን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከለውጡ በፊት በከባድ የዕዳ ጫና ውስጥ እንደነበረች ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በተለይም ቀደም ሲል ይወሰድ የነበረው የንግድ ብድር ለሀገሪቱ ትልቅ ፈተና ሆኖ እንደነበር ጠቁመዋል። ይህ ዓይነቱ ብድር የሀገሪቱን የፋይናንስ አቅም ያዳከመና አበዳሪዎች ተጨማሪ ብድር ለመስጠት እንዲጠራጠሩ ያደረገ መሆኑንም አስታውሰዋል። የሌብነት መስፋፋት እና የፕሮጀክቶች አፈጻጸም ድክመት ችግሩን ይበልጥ አወሳስቦት እንደነበርም አንስተዋል። ይሁን እንጂ ከለውጡ በኋላ ኢትዮጵያ የዕዳ ጫናዋን ከመቀነስ ባለፈ አንድም የንግድ ብድር አለመውሰዷን ጠቁመዋል። ይህ እርምጃ ምስጋና የሚገባው ጠንካራ የፖሊሲ አቅጣጫ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ቀድሞ የተወሰዱ የንግድ ብድሮችን ወደ መደበኛ ብድር ለመቀየር የተደረጉ ድርድሮች ስኬታማ መሆናቸውን አንስተዋል።