ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jan 26, 2026 80
ጂንካ፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፡- የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባዔ አለማየሁ ባውዲ ገለፁ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባዔ አለማየሁ ባውዲ የተመራ ቡድን በደቡብ ኦሞ ዞን አርብቶ አደር አካባቢዎች የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን ዛሬ ተመልክቷል።   ቡድኑ በዞኑ በናፀማይ ወረዳ በክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ የተገነቡ የእንስሳት ግብይትና የኤክስፖርት እንስሳት ማሰባሰቢያ ማዕከላት፣ ትምህርት ቤቶችና የመንገድ መሰረተ ልማቶችን ጨምሮ ሌሎች ፕሮጀክቶችን ተመልክቷል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ አለማየሁ ባውዲ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፣ በአርብቶ አደሩ አካባቢ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች አበረታች በመሆናቸው ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል።   በአርብቶ አደሩ አካባቢ የተገነቡ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከላት ህገወጥ የቁም እንስሳት ንግድን በመከላከል ህጋዊ ንግድን ስለሚያጠናክር አርብቶ አደሩ እንስሳቱን በተሻለ ዋጋ በመሸጥ ተጠቃሚ እንዲሆን ያስችላል ብለዋል። አርብቶ አደሩን በማህበር በማደራጀት በከብት ማድለብ፣ በእርሻ ሥራና በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ሥራዎች በማሳተፍ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ የተጀመሩ አበረታች ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም አሳስበዋል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አከባቢ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር በበኩላቸው መንግስት የክልሉን አርብቶ አደሮች ተጠቃሚነት ለማሳደግና የድርቅ ተጋላጭነታቸውን ለመቀነስ የሚያስችሉ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በበና ፀማይ ወረዳ የተከናወኑ የእንስሳት ግብይት ማዕከል፣ የመንገድ መሰረተ ልማቶች እና ትምህርት ቤቶችን በአብነት ጠቁመዋል። የበና-ፀማይ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ዮሐንስ ጋርሾ በበኩላቸው የተከናወኑት የልማት ፕሮጀክቶች የረጅም ዓመታት የአርብቶ አደሩ የልማት ጥያቄዎች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በቀጣይም በወረዳው አርብቶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ይበልጥ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።   ቡድኑ በነገው እለትም በሐመር፣ በኛንጋቶም እና በዳሰነች ወረዳዎች ህዝብን ተጠቃሚ ለማድረግ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችንም እንደሚመለከት ታውቋል።    
በክልሉ ጥራትና ደህንነታቸው የተረጋገጠ የግብርና ግብዓቶችና ቴክኖሎጂዎች ለአርሶአደሩ ተደራሽ እየተደረጉ ነው
Jan 26, 2026 67
ባህር ዳር፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ጥራትና ደህንነታቸው የተረጋገጠ የግብርና ግብዓቶችና ቴክኖሎጂዎች ለአርሶአደሩ ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። የአማራ ክልል የግብርና ጥራትና ቁጥጥር ባለስልጣን የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት የዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ በባህር ዳር እየተካሄደ ይገኛል።   የቢሮው ምክትል ሃላፊ አጀበ ስንሻው በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ ምርትና ምርታማነትን የበለጠ ማሳደግ የሚያስችሉ የጥራት ደረጃቸው የተረጋገጠ የግብርና ግብዓቶችና የቴክኖሎጂ ውጤቶች ለአርሶአደሩ እየቀረቡ ነው። አርሶአደሩ ጥራታቸው የተረጋገጠ ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በወቅቱ እንዲያገኝ የሚደረገው ቁጥጥር ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። የግብርና ግብዓቶችንና ቴክኖሎጂን ተደራሽ ማድረግ ምርታማነትን በዘላቂነት ከማሳደግ ባለፈ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶች ለማስጠበቅ ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል።   የክልሉ የግብርና ጥራትና ቁጥጥር ባስልጣን ዋና ዳይሬክተር ፈንታሁን ስጦታው በበኩላቸው፤ የግብርና ምርቶች ጥራትን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ቁጥጥርና ክትትል አየተደረገ ነው ብለዋል። ምርጥ ዘርን ጨምሮ ሌሎች የግብርና ግብዓቶች ከምርት ሂደት ጀምሮ በማጓጓዝና በክምችት ወቅት ሊያጋጥማቸው የሚችለውን የጥራት ጉድለት ለመፍታት በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። በዘርፉ የተጀመሩ ተግባራት አበረታች እንደሆኑ አንስተው፤ የበለጠ ውጤታማ ለማድረግም የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ አሰራር ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።   የኢትዮጵያ ግብርና ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወንዳለ ሃብታሙ (ዶ/ር) ባለስልጣኑ ለሀገር ወስጥና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ የግብርና ምርቶች ላይ በቴክኖሎጂ የታገዘ ቁጥጥር እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በ2017 እና 2018 በጀት ዓመት በአማራ ክልል ብቻ ቦለቄ፣ ሰሊጥና ሌሎች ምርቶችን ወደ ወጭ ገበያ ለሚያቀርቡ ከአንድ ሺ በላይ ድርጅቶች የምርት ጥራት ማረጋገጫ መሰጠቱን አመልክተዋል። የጥራት ክትትልና ቁጥጥር ስራዎች መጠናከርም የዘርፉን ዘላቂ እድገት ከማረጋገጥ ባሻገር በሰው፣ በእንስሳትና በእፅዋት ሊከሰቱ የሚችሉ ጉዳቶችን ለመከላከል እንደሚያስችል በማንሳት። ለሁለት ቀናት በሚቆየው በዚሁ መድረክ በየደረጀው የሚገኙ የዘርፉ አመራሮችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛል።  
የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የልማት አጀንዳ የሚያደርገውን ድጋፍ በዘላቂነት ለመቀጠል ቁርጠኛ ነው - የባንኩ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዌንቻይ ዣንግ
Jan 26, 2026 100
አዲስ አበባ፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፦ የዓለም ባንክ የኢትዮጵያን የልማት አጀንዳ በዘላቂነት ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን የባንኩ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዌንቻይ ዣንግ ገለጹ። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ከዓለም ባንክ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዌንቻይ ዣንግ ጋር ተወያይተዋል። የገንዘብ ሚኒስትሩ በውይይቱ ላይ ለማኔጂንግ ዳይሬክተሩ ኢትዮጵያ ተግባራዊ እያደረገች የምትገኘውን የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ፕሮግራምን አስመልክቶ ገለጻ አድርገዋል።   የሪፎርም ፕሮግራሙ ኢኮኖሚውን በግሉ ዘርፍ እንዲመራ የማድረግ፣ የኢኮኖሚ እድገት ምንጮችን ማስፋት፣ ዲጂታል ኢኮኖሚና ቱሪዝምን ማሳደግ እንዲሁም በአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና አማካኝነት ቀጣናዊ ትስስር የማጠናከር ግብ እንዳለው አመልክተዋል። ሚኒስትሩ የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ ቁልፍ ዘርፎች እያደረገ ያለውን ድጋፍ እና የኢትዮጵያ ሪፎርምና የልማት የትኩረት መስኮች ላይ ያለውን ወሳኝ ሚና አድንቀዋል። የዓለም ባንክ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ዌንቻይ ዣንግ የኢትዮጵያ መንግስት የእዳ እንደገና ማዋቀርን ጨምሮ በማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ የወሰዳቸውን ጠንካራ እርምጃዎች ያደነቁ ሲሆን የተገኙ ለውጦችም አበረታች መሆናቸውን ተናግረዋል። የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የልማት አጀንዳ በተለያዩ የፋይናንስ አማራጮች አማካኝነት የሚያደርገውን ዘላቂ የቴክኒክ እና ፋይናንስ ድጋፍ አጠናክሮ ለመቀጠል ቁርጠኛ መሆኑንም ገልጸዋል።   ሁለቱ ወገኖች በውይይታቸው የኢትዮጵያ እና ዓለም ባንክ ስትራቴጂካዊ አጋርነት የደረሰበትን ደረጃ ገምግመዋል። በተለይም ከኢትዮጵያ የልማት ግቦች ጋር በተጣጣመ ሁኔታ በባንኩ በኩል እየተደረጉ ያሉ የበጀት ድጋፎችና የፕሮጀክት ፋይናንስ አቅርቦት ላይ መምከራቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
 የህዝብን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ በተከናወኑ ሥራዎች ውጤት ተመዝግቧል - አቶ ገብረመስቀል ጫላ
Jan 26, 2026 94
ወላይታ ሶዶ፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ በተከናወኑ ሥራዎች በየዘርፉ ውጤት መመዝገቡን የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ ገለጹ። የወላይታ ዘመን መለወጫ ጊፋታ በዓል በዩኔስኮ መመዝገቡን በማስመልከት "የጊፋታ ብስራቶች ለሕዝባችን ከፍታ" በሚል መሪ ሃሳብ በወላይታ ሶዶ ከተማ የተዘጋጀ ሲምፖዚየምና የፓናል ውይይት ተካሂዷል። ውይይቱ የተካሄደው የወላይታ ልማት የተቀናጀ የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ላይ በማተኮር ነው።   በመድረኩ ላይ የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ እንደገለጹት፤ የወላይታ የዘመን መለወጫ በዓል "ጊፋታ" በዩኔስኮ እንዲመዘገብ የረጅም ጊዜ ጥያቄ እንደነበር አስታውሰው፣ በቅርቡ መመዝገቡ በአካባቢው ላይ ከፍተኛ መነቃቃት ፈጥሯል ብለዋል። ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ለህዝብ ባህል፣ ወግና የልማት ጥያቄዎች ትኩረት መሰጠቱን አስታውሰው፣ በዚህም በክልሉ በተለያዩ የልማት ዘርፎች ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ተመዝግበዋል ብለዋል። የወላይታ ዘመን መለወጫ በዓል "ጊፋታ" ያሉትን እሴቶች በማጎልበትና የህዝብን አንድነት በማስቀጠል በየዘርፉ የልማት ግቦችን ለማሳካትና ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚሰራ አመልክተዋል።   ለዚህም በየአካባቢው ያሉትን ፀጋዎች ለይቶ በማልማት ለህዝብ ተጠቃሚነት ለማዋል መረባረብ እንደሚገባ አሳስበዋል። "ጊፋታ" ተገቢ እውቅና እንዲያገኝ የባህልና ቋንቋ ሲምፖዚየሞች ሲዘጋጁ እና ምሁራንም በጉዳዩ ላይ ጥናት ሲያካሂዱ መቆየታቸውን የገለጹት ደግሞ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ ናቸው። "ጊፋታ" በዩኔስኮ እንዲመዘገብ አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል።   የዞኑ አስተዳደር የህዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በየደረጃው ለመፍታት በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና በፖለቲካው ዘርፍ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል። የዞኑን ገቢ ለማሳደግ በተደረገ ጥረት በ2018 ዓ.ም የመጀመሪያ ስድስት ወር ብቻ 2 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር መሰብሰቡንም ጠቅሰዋል። በዞኑ ከ10 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ 320 ባለሃብቶች በግብርና፣ በኢንዱስትሪና በአገልግሎት ዘርፎች የተሰማሩ ሲሆን፣ ለ42 ሺህ 397 ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ እድልም እንደተፈጠረ ገልጸዋል። በትምህርት፣ በጤና እና በሌሎችም ዘርፎች ህዝቡን የተሻለ ተጠቃሚ ለማድረግ በተለየ ትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ነው ዋና አስተዳዳሪው የገለጹት። በተለያዩ ዘርፎች የህዝብን ተጠቃሚነት አጠናክሮ ለማስቀጠል የወላይታ ልማት የተቀናጀ የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ሥራ መጀመሩንም አንስተዋል።   የወላይታ ሶዶ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ መንግስቱ ትግሮ በበኩላቸው፤ ጊፋታ በዩኔስኮ መመዝገቡ በከተማው በፈጠረው መነቃቃት የቱሪስት ፍሰት እየጨመረ መጥቷል። የቱሪስቶችን የቆይታ ጊዜ ለማራዘምም የመዳረሻ ስፍራዎች ልማትና የጸጥታ ሥራ ከሌላው ጊዜ በተለየ መልኩ እየተመራ መሆኑን አመልክተዋል። በመድረኩ የፌደራል፣ የክልል፣ የዞንና ከተማ አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
በመዲናዋ በሁሉም መስኮች የተመዘገቡ ስኬቶችን በማስቀጠል ለዜጎች ተጠቃሚነት በትኩረት ይሰራል
Jan 26, 2026 65
አዲስ አበባ፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ በሁሉም መስኮች የተመዘገቡ ስኬቶችን በማስቀጠል ለዜጎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በትኩረት እንደሚሰራ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ''በትጋት አዲስ አበባን ወደ ላቀ ስኬት” በሚል መሪ ሀሳብ በዓድዋ ድል መታሰቢያ ሲያካሂድ የቆየው የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የመንግስትና የፓርቲ ሥራዎች አፈፃፀም ግምገማ ተጠናቅቋል። የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማጠቃለያ መድረኩ ወቅት፤ መዲናዋን ውበትና ጸዳል ያላበሱ ዘመናዊ የመንገድ፣ የውሃ፣ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውን አስታውቀዋል። አዲስ አበባ ከተማን ለማስዋብ የተከናወኑ የልማት ስኬቶችም የመዲናዋን የኮንፈረንስ ማዕከልነት በማሳደግ በርካታ ዜጎች በቱሪዝም ዘርፍ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማስቻሉን ገልጸዋል። በመሶብ የአንድ ማዕከል የተከናወኑ ተግባራትም የዜጎችን የመልካም አስተዳደር ፍላጎት ምላሽ በመስጠት የአገልግሎት እርካታ እየተፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል።   በበጎ ፈቃድ አገልግሎትም የልማት አጋሮችና የህዝብን ተሳትፎ በማሳደግ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን አስረድተዋል። በ2018 በጀት ዓመት በሰው ተኮር ልማት፣ በገበያ የምርት አቅርቦት ሥርዓት፣ በገበያ ማረጋጋትና ኑሮ ውድነት ቅንሳ፣ በዘላቂ ሰላም ግንባታና ተያያዥ የልማት መስኮችም አስደናቂ ስኬት ማምጣት እንደተቻለ አንስተዋል። በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራት በሁሉም ዘርፎች የተገኙ የልማት ስኬቶችም የአመራር ቁርጠኝነትና ተቀናጅቶ የመስራት ውጤት መሆኑን አብራርተዋል። በሚቀጥሉት በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራትም የህዝብን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በላቀ የመፈጸም አቅም የልማት ስኬቶችን ለማስቀጠል እንደሚሰራ አቅጣጫ ሰጥተዋል። የከተማ አስተዳደሩ አመራርም የመፈጸም አቅምን የበለጠ በማጎልበት በቤት ልማት፣ ቱሪዝም፣ መልካም አስተዳደር ስራዎችንና ገቢ አሰባሰብን በማጠናከር የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማስቀጠል በትኩረት መስራት እንደሚጠበቅ አሳስበዋል።
ኢትዮጵያ ለጀመረችው አረንጓዴ የኢኮኖሚ ሽግግር አስተማማኝ የኃይል አቅርቦት ወሳኝ ነው
Jan 26, 2026 98
አዲስ አበባ፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለጀመረችው አረንጓዴ የኢኮኖሚ ሽግግር አስተማማኝና ተመጣጣኝ የኃይል አቅርቦት ወሳኝ መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) ገለፁ። የቻይና ሳውዘርን ፓወር ግሪድ ቴክኖሎጂ እና የኤዳን ኤሌክትሮ ፓወር ግሩፕ ኢትዮጵያን የምስራቅ አፍሪካ የአረንጓዴ ቴክኖሎጂ ማዕከል የማድረግ ዓላማን የሰነቀ ስትራቴጂካዊ አጋርነት መስርተዋል። የአጋርነት ስምምነቱን የኤዳን ኤሌክትሮ ፓወር ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ እድሪስ አደም እና የቻይና ሳውዘርን ፓወር ግሪድ ቴክኖሎጂ ኩባንያ ከፍተኛ ተወካይ ዣኦ ዚዪ ተፈራርመዋል።   የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ በዘመናዊ መልክ ለጀመረችው ኢኮኖሚያዊ ሽግግር አስተማማኝ እና ተመጣጣኝ የኃይል አቅርቦት ወሳኝ ነው። ኃይል የኢንዱስትሪ ልማት ሞተር ብቻ ሳይሆን፣ ለዲጂታል ኢትዮጵያ ግንባታ መሰረት መሆኑን ገልጸው፤ ያለ ኤሌክትሪክ አቅርቦት ፈጠራን ማስፋፋትም ሆነ አገልግሎትን ተደራሽ ማድረግ እንደማይቻልም ተናግረዋል። በመሆኑም ኢትዮጵያ በብሔራዊ የኃይል መስመር ላይ ብቻ ጥገኛ ሳትሆን ሚኒ-ግሪድ እና ሃይብሪድ የታዳሽ ኃይል ሥርዓቶችን ለማስፋፋት እየተሰራ ነው ብለዋል። ይህም በገጠር የሚገኙ ስራ ፈጣሪዎችና ማህበረሰቦችም እኩል የዲጂታል ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። በኤዳን ኤሌክትሮ ፓወር ግሩፕ እና በቻይና ሳውዘርን ፓወር ግሪድ ቴክኖሎጂ መካከል የተመሰረተው አጋርነት ዘመናዊ የኃይል ማከፋፈያና ማከማቻ ቴክኖሎጂዎችን ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባት ያስችላል ብለዋል። የኃይል መፍትሔ መሣሪያዎችን በሀገር ውስጥ የመገጣጠም እና የማምረት አቅምን ለማሳደግ እንዲሁም ለኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች የቴክኖሎጂ ስልጠና ለመስጠት እድል እንደሚፈጥርም ነው የገለፁት።   የሀገር ውስጥ አቅምን ለመገንባት ለሚሰሩ ኩባንያዎች መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋልም ብለዋል። የኤዳን ኤሌክትሮ ፓወር ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ እድሪስ አደም በበኩላቸው፣ ኤዳን ፓወር በኢትዮጵያ የሀይል እድገት ውስጥ ለ20 ዓመታት አጋር ሆኖ መቆየቱን ተናግረዋል። ስምምነቱ የኢትዮጵያን ፍላጎት ለማሟላት፣ በንግድ እና ኢንቨስትመንት በጋራ ለመስራት ትልቅ ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል ብለዋል። የቻይና ሳውዘርን ፓወር ግሪድ ቴክኖሎጂ ኩባንያ ከፍተኛ ተወካይ ዣኦ ዚዪ እንዳሉት፣ይህ አጋርነት የቻይናን ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ከኢትዮጵያ ተጨባጭ ፍላጎት ጋር ለማጣጣም የሚያስችል ነው።
ሰብላችንን በወቅቱ ሰብስበን በማጠናቀቅ ወደ ቀጣይ ተግባራት ተሸጋግረናል - አርሶአደሮች
Jan 26, 2026 60
ደብረ ማርቆስ፤ ጥር 18 /2018 (ኢዜአ)፡- በመኸር ያለሙትን ሰብል በወቅቱ ሰብስበው በማጠናቀቅ ወደ ሌሎች የመስኖ እና እንስሣት ዕርባታ ተግባራት መሸጋገራቸውን የምሥራቅ ጎጃም ዞን አርሶአደሮች ተናገሩ። በዞኑ የአዋበል ወረዳ ወጀል ቀበሌ እንዲሁም የአነደድ ወረዳ እነችፎ ቀበሌ አርሶአደሮች ምሥጋናው የኔው እና አጉማሱ አታላይ እንዳሉት፤ በመኸር እርሻ ያለሙትን ሰብል በወቅቱ መሰብሰባቸው በዝናብ እንዳይበላሽና የምርት ብክነት እንዳከሰት አስችሏል።   የደረሱ ሰብሎችን በደቦ በወቅቱ መሰብሰብ አርሶአደሩ ጊዜን በአግባቡ እንዲጠቀምና ምርትና ምርታማነቱ እንዲጨምር የጎላ ሚና እንዳለውም አስገንዝበዋል። የመኸር ሥራን በማጠናቀቃቸው ወደ መስኖና እንስሣት ዕርባታ ሥራ መሸጋገራቸውንም ለኢዜአ አረጋግጠዋል።   በዞኑ በመኸር ከተሸፈነው ከ640 ሺህ ሔክታር በላይ ማሳ ከ625 ሺህ ሔክታር የሚልቀው ሰብል መሰብሰቡን በዞኑ ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ቡድን መሪ እምቢአለ አለኸኝ አስታውቀዋል።   ቀሪው በሁለት ሳምንታት ውስጥ ተሰብስቦ እንደሚጠናቀቅም አመላክተዋል። የምርት ብክነት እንዳይኖር በሜካናይዜሽና በሰው ኃይል በጥንቃቄ ምርት መሰብሰቡን ጠቁመዋል። በምርት ዘመኑ ከለማው ሰብል ከ25 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅም ነው የገለጹት።
በመዲናዋ የተገነቡ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ናቸው
Jan 25, 2026 129
አዲስ አበባ ፤ጥር 17/2018 (ኢዜአ)፡-በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራት በመዲናዋ የተገነቡ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተለያዩ ተቋማት ገለጹ:: የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት የመጀመሪያ ግማሽ ዓመት የዕቅድ አፈፃጸምና የቀጣይ የትኩረት መስኮች የግምገማ ምክክር መድረክ ሁለተኛ ቀን ውሎ መካሄዱን ቀጥሏል። በሁለተኛው ቀን ውሎው የግምገማ የምክክር መድረክ ተሳታፊ የከተማ አስተዳደሩ የተለያዩ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች የመዲናዋን ዕድገት የሚያስቀጥሉ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ቅድስት ወልደጊዮርጊስ፤በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራት የመኖሪያ ቤቶችን በመገንባት ነዋሪዎችን ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል ተጨባጭ ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል። የመዲናዋን ነዋሪዎች የቤት አቅርቦት ፍላጎት ለማጣጣም በመንግስት የግል አጋርነት፣ በማኅበር ፤በሪል ስቴትና በግል የቤት ልማት አማራጭ በማስፋት በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በተለያዩ አማራጮች በመዲናዋ የተገነቡና በግንባታ ሂደት የሚገኙ የቤት ልማት ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን የቤት አቅርቦት ፍላጎት ምላሽ በመስጠት ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሙህዲን ረሻድ፤ በበጀት ዓመቱ የመዲናዋን የትራንስፖርት ሥርዓት የሚያሳልጥ የመንገድ መሰረተ ልማት መገንባቱን ገልጸዋል። በሚቀጥሉት የበጀት ዓመቱ ስድስት ወራትም በግንባታ ሂደት የሚገኙ የመንገድ ፕሮጀክቶችን በተሻለ ፍጥነትና ጥራት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራ ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ዘሪሁን አባተ እንደገለጹት፤ የመዲናዋን የንፁሕ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ፍላጎት ምላሽ መስጠት የሚያስችል መሠረት መጣሉን ገልጸዋል። በቀጣይም አዳዲስ የውሃ ፕሮጀክቶችን ተግባራዊ በማድረግና ነባር የውሃ ፕሮጀክቶችን ደረጃና ጥራት በማሻሻል የውሃ አቅርቦት አቅምን የማሳደግ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል
Jan 25, 2026 132
ወላይታ ሶዶ፤ ጥር 17/2018(ኢዜአ)፦ የህብረተሰቡን የጋራ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ እና የወላይታ ልማት ማህበር ስራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ገብረመስቀል ጫላ አስታወቁ። የልማት ማህበሩ 25ኛ ዓመት ጠቅላላ መደበኛ ጉባኤ በወላይታ ሶዶ ከተማ እያካሄደ ይገኛል።   አቶ ገብረመስቀል ጫላ በጉባኤው እንደገለጹት ጠንካራ የስራ ባህል በማስረጽ የህዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ማህበሩ ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየሰራ ይገኛል። ማህበሩ በተለይም የህብረተሰቡን የጋራ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጡ የልማት ስራዎች ላይ ትኩረት መስጠቱን ጠቁመዋል። በቀጣይም የህብረተሰቡን አንድነት በበለጠ በማጠናከር ተግባሩን ማስቀጠል እንደሚገባው አመላክተዋል።   ግብርናን በማዘመን ህዝቡን ከጠባቂነት ለማውጣትና የተሻለ ኑሮ እንዲመራ እየተደረገ ያለው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስገንዝበዋል። ማህበሩ የያዘው ራዕይ እንዲሳካ በጋራ መሥራት እንደሚገባ ጠቁመው ለልማት ማህበሩ መጠናከር ድጋፍ እያደረጉ ያሉ አካላትን አመስግነዋል። ልማት ማህበሩ መንግስት እያከናወነ ያለውን ስራ በማገዝ ለህዝቡ ልማት የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ይገኛል ያሉት ደግሞ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ሳሙኤል ተሰማ ናቸው።   በለውጡ መንግሥት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የተቋቋሙለትን ዓላማ እንዲያሳኩ ምቹ ምህዳር መፈጠሩን አንስተው ቀጣይነት ያለው ውጤት እንዲያስመዘግብ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ማህበሩን በዘላቂነት ለማጠናከር በህዝቡ ተሳትፎ እና በአጋር ተቋማት ትብብር ከ650 ሚሊየን ብር በላይ ለማሰባሰብ መታቀዱን አስታውቀዋል። የልማት ማህበሩ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አበባየሁ ቶራ(ዶ/ር) በበኩላቸው ማህበሩ ከአባላቱ፣ ከህዝቡና አጋር አካላት በሚገኝ የገንዘብ ድጋፍ የህዝቡን የልማት ፍላጎት ለማሟላት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   የልማት ማህበሩ በትምህርት፣ በጤና፣ በዘላቂ የኑሮ ማሻሻያ እና በሰው ሀብት ልማት ዙሪያ የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ጠቁመው ለማህበሩ ውጤታማነት የባለድርሻ አካላት ድጋፍ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።
የሌማት ትሩፋትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ለማር ምርታማነት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው
Jan 25, 2026 134
አዲስ አበባ፤ ጥር 17/2018(ኢዜአ)፦የሌማት ትሩፋትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ለማር ምርታማነት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ግብርና ሚኒስቴር ገለፀ። የኢትዮጵያ ምቹ የአየር ጠባይና የአረንጓዴ አሻራ የደን ሽፋን ዕድገት የበርካታ ዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደገ ይገኛል። በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና ዓሳ ሃብት ዘርፍ ሚኒስትር ደኤታ አማካሪ ግርማ ሙሉጌታ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የግብርና ምርታማነትን ማሻሻል መርሃ ግብሮች በማር ምርታማነት ላይ እመርታዊ ውጤት እያስገኘ ነው። በተለይም የሌማት ትሩፋትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች የዜጎችን የንብ ማነብ ተነሳሽነት በማሳደግ በማር ምርታማነት ላይ ከፍተኛ ውጤት አንዲመዘገብ እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል።   የኢትዮጵያ የማር ምርታማነትም ዜጎች የተመጣጠነ የምግብ ሥርዓት የሚያገኙበትን አማራጭ በመፍጠር የውጭ ምንዛሬ ገቢ ጭምር እያስገኘ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም የዜጎችን የንብ ማነብ የሥራ ባህል በማሳደግ የማር ምርታማነትን ማሻሻል የሚያስችል ምኅዳር የመፍጠር ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አንስተዋል። በማር ምርታማነት ለተመዘገበው ስኬትም የንብ አናቢዎች ዘመናዊ የአመራርት ዘዴ የግንዛቤ ማስጨበጫና የግብዓት አቅርቦት መሻሻል ጉልህ ሚና እየተወጣ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዚህም ባለፈው በጀት ዓመት 326ሺህ ሜትሪክ ቶን የማር ምርት በመሰብሰብ በተያዘው በጀት ዓመት 375 ሺህ ሜትሪክ ቶን የማር ምርት ለመሰብሰብ በተያዘው ዕቅድ መሠረት አበረታች ውጤት መገኘቱን ገልጸዋል። የማር ምርት በጥራትና በብዛት በማምረት የውጭ ገበያ የማር ምርት አቅምን ለማሳደግ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝም አብራርተዋል።   የኢትዮጵያ ንብ ሃብት ማኅበር ዋና ሥራ አስኪያጅ ነጋሽ በቃና በበኩላቸው፤ መንግስት ለግብርና ምርታማነት የሰጠው ትኩረት በማር ምርታማነት ላይ ውጤት እንዲገኝ እያስቻለ ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራና የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብሮችም በርካታ ዜጎች በንብ ማነብ የሥራ መስክ በመሰማራት የማር ምርታማነት ለኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የድርሻውን እንዲወጣ እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል።    
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ የራስን ተፈጥሯዊ፣ ሕጋዊ፣ መልክዓ-ምድራዊና ታሪካዊ ሃብት ምላሽ የማስገኘት ምክንያታዊ የሕልውና ጉዳይ ነው
Jan 25, 2026 197
አዲስ አበባ፤ ጥር 17/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ የራስን ተፈጥሯዊ፣ ሕጋዊ፣ መልክዓ-ምድራዊና ታሪካዊ ሃብት ምላሽ የማስገኘት ምክንያታዊ የሕልውና ጉዳይ መሆኑን ምሁራነ ገለጹ። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቂያና የጋራ ትርክት መገንቢያ መሆኑንም የተናገሩት። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ መልክዓ-ምድራዊና ኢኮኖሚያዊ የህልውና ጥያቄ መሆኑ ይታወቃል። በኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ዙሪያ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ ምሁራንም፤ ኢትዮጵያ የባሕር በሯን እንድታጣ የተደረገችበት ታሪካዊ ሴራ የሚያስቆጭ መሆኑንም ገልጸዋል።   የባህልና ታሪክ ተመራማሪው ፕሮፌሰር አህመድ ዘካርያ፤ የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ማንነትና ስልጣኔ ከቀይ ባሕር ባለቤትነት ጋር በእጅጉ ጥብቅ ቁርኝት አለው ብለዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄም የራስን ተፈጥሯዊ፣ ሕጋዊ፣ መልክዓ-ምድራዊና ታሪካዊ ሃብት ምላሽ የማስገኘት ምክንያታዊ የሕልውና ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ምላሽ የማስገኘት ቀጣናዊና አሕጉራዊ ሰላምና ደኅንነትን በማስጠበቅ ለፍትሐዊ የጋራ ተጠቃሚነትና ዕድገት መሠረት እንደሚሆን ተናግረዋል። ኢትዮጵያውያንም የሀገራቸውን ሉዓላዊነት፣ ብሔራዊ ጥቅምና ፍላጎት የሚያስከብሩ ጽኑ ህዝቦች መሆናቸውን የዓድዋ ድል ሕያው ምስክር መሆኑን አስታውሰዋል። የጋራ ተግባቦት ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማሸጋገር ዓይነተኛ ሚና አለው ያሉት ምሁሩ፤ አሰባሳቢ ትርክት ግንባታም የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። በዚህም የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ለማስገኘት በሚደረገው ጥረት ሁሉም ዜጋ በከፍተኛ የኃላፊነት መንፈስ በመተባበር ለሀገር ብሔራዊ ጥቅም መከበር መስራት እንደሚኖርበት አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅትም የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ምላሽ ለማስገኘት የሚደረገው ጥረት የሀገርን ዕድገትና ቀጣዩን ትውልድ ታሳቢ ያደረገ ወሳኝ ብሔራዊ አጀንዳ መሆኑንም አስረድተዋል።   በውጪ ጉዳይ ኢኒስቲትዩት የአፍሪካ ጉዳዮች ተመራማሪ ጋሻው አይፈራም(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ታሪክና ስልጣኔ ከባሕር በር ባለቤትነት ጋር የተሰናሰለ ነው ብለዋል። ለአብነትም ከአክሱም ዘመነ መንግሥታት ጀምሮ ለበርካታ ሺህ ዘመናት ያህል ቀይ ባሕር የኢትዮጵያ የተፈጥሮ ወሰንና የግዛት መዳረሻ አካል ሆኖ እንደቆየ አስታውሰዋል። በታሪካዊ ጠላቶች ሴራ እና የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም በቅጡ ባልተገነዘቡ ውስን ቡድኖች አማካኝነት ኢትዮጵያ ከተፈጥሯዊ የባሕር በር ወሰኗ እንድትገለል መደረጉን አስታውሰዋል። በዚህም የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ሕጋዊ፣ ሥነ-ልቦናዊ፣ መልክዓ-ምድራዊ እና ፍትሕዊ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን መሰረት ያደረገ ትክክለኛና ምክንያታዊ ጥያቄ መሆኑን ተናግረዋል።
በድሬዳዋ በበጀት አመቱ ስድስት ወራት ከ48 ቢሊየን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች ወደ ስራ ገብተዋል
Jan 25, 2026 84
ድሬዳዋ፤ ጥር 17/2018(ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ አስተዳደር በተያዘው በጀት ዓመት ያለፉት ስድስት ወራት ከ48 ቢሊየን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች ወደ ስራ መግባታቸውን የንግድ ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ። በከተማ አስተዳደሩ የተከናወኑ የኮሪደር ልማትና መሠረተ ልማት ስራዎች የኢንቨስትመንት ፍሰቱ እንዲጨምር ከፍተኛ ሚና እያበረከቱ ናቸው።   በቢሮው የኢንቨስትመንት ፕሮጀክት ጥናት መረጃ ዝግጅት ቡድን መሪ አበራ መንግሥቱ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በበጀት አመቱ ስድስት ወራት ከ48 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ 251 የሀገር ውስጥ እና የውጭ ባለሃብቶች ፈቃድ ወስደው ወደ ስራ ገብተዋል። ፈቃድ ከወሰዱ አልሚዎች መካከል በእስካሁኑ እንቅስቃሴ 10 የሚሆኑት ኢንዱስትሪዎች ማምረት መጀመራቸውንና ለ1ሺህ 800 ዜጎች የስራ እድል መፍጠራቸውን ተናግረዋል። በግማሽ በጀት ዓመቱ ወደ ስራ የገቡ አልሚዎችም በማኑፋክቸሪንግ፣ በአገልግሎት፣ በኮንስትራክሽንና በግብርና ዘርፎች መሰማራታቸውን ገልጸው በዚህም ከ13 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዚያዊ የስራ ዕድል ይፈጥራሉ ብለዋል። እንደ አቶ አበራ ገለፃ ድሬዳዋ ለጅቡቲ ወደብ ያላት ቅርበት፣ አስተማማኝ ሰላምና ፀጥታ እንዲሁም በፌዴራል እና በአስተዳደሩ ለባለሃብቶች የሚደረገው ድጋፍ ለኢንቨስትመንት ፍሰቱ መጨመር አስተዋጽኦ እያበረከቱ ናቸው። እንዲሁም ባለፉት የለውጥ አመታት የተዘረጉ መሠረተ ልማቶች፣ የኮሪደር ልማት እና ነፃ የንግድ ቀጣናው ለኢንቨስትመንት ስራ የሚመጡ የውጭና የሀገር ውስጥ ባለሃብቶች በከፍተኛ ደረጃ እንዲጨምሩ ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውን ገልጸዋል።   በድሬዳዋ ኢንቨስት ለሚያደርጉ ባለሃብቶች ልዩ ድጋፍ መደረጉን የተናገሩት ደግሞ የአስተዳደሩ የመሬት ልማትና ማኔጀመንት ቢሮ ኃላፊ ሳጅድ አልይ ናቸው። ባለሃብቶች የሚሰጣቸውን መሬት ለታለመለት አላማ በፍጥነት እንዲያውሉ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ እንደሚገኝም ጨምረው ተናግረዋል። የኤ ኤም ሞተርስ የመኪና መገጣጠሚያ ኢንዱስትሪ ስራ-አስኪያጅ አለማየሁ ሚደቅሳ፤ በተሰጣቸው ምቹ ቦታ የከባድ መኪና እና ለህዝብ ትራንስፖርት የሚውሉ የኤሌክትሪክ መኪናዎችን ለመገጣጠም መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።
በሐረሪ ክልል የተዘረጉ ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥና የልማት ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት እያጎለበቱ መጥተዋል
Jan 25, 2026 240
ሐረር ፤ጥር 17/2018(ኢዜአ)፡- በሐረሪ ክልል የተዘረጉ ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥና የልማት ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት እያጎለበቱ መምጣታቸውን ነዋሪዎች ተናገሩ። የህዝቡን የልማትና የአገልግሎት አሰጣጥ ተግባራት በቅንጅት በማከናወን የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ተናግረዋል። የሐረሪ ክልል ፐብሊክ ሰርቪስ እና ሰው ሃብት ቢሮ በመልካም አስተዳደር ዙሪያ ህዝባዊ መድረክ አካሂዷል።   የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው በክልሉ የተከናወኑ የልማትና የአገልግሎት አሰጣጥ ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል። ከተሳታፊዎቹ መካከል አቶ ኡስማን ዩስፍ እንዳሉት በክልሉ ህዝቡን በማሳተፍ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የነዋሪውን ተጠቃሚነት እያጎለበቱ መሆናቸውን ተናግረዋል። በከተማዋ የተከናወኑ እንደ ኮሪደር ልማት ስራዎች እና ሌሎች ልማቶች የህዝቡን ጥያቄ የመለሱ በመሆኑ እንዲጠናከሩ ጠይቀዋል። የነዋሪው ጥያቄ የነበሩ የመንገድና የኤሌክትሪክ አገልግሎት መፍትሄ አግኝተዋል ያሉት ደግሞ ወይዘሮ ፋንቱ እሸቱ ናቸው።   ከተማዋን ውብ እና ለጎብኚውም ሆነ ለነዋሪዎች ምቹ በማድረግ የቱሪስት ፍሰቱ እንዲጨምር በማድረጉ ለስራ እድል ፈጠራና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እየተሳለጡ መሆናቸውን ያወሱት ደግሞ ሻምበል ጋሻው ሙሉዓለም ናቸው። ይህም ተግባር የክልሉ አመራርና የህዝብ ቅንጅት ውጤት በመሆኑ በቀጣይም በትራንስፖርት አገልግሎት አሰጣጥና የዋጋ ንረትን የሚያባብሱ ነጋዴዎችን መቆጣጠር ላይ መጠናከር እንዳለበት ጠይቀዋል።   በክልሉ በማህበረሰብ ጤና መድህን እየተከናወነ የሚገኘው ስራ አቅመ ደካሞችን እያገዘ መሆኑንና በፍትህ አገልግሎት አሰጣጥም ይስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን በመቅረፋቸው ሊበረታቱ ይገባል ያሉት ደግሞ ወይዘሮ ሳራ ይስሃቅ ናቸው።   በቀጣይም ያልተገባ ዋጋ በሸቀጦች ላይ በመጨመር ህዝቡን ለምሬት እየዳረጉ የሚገኙትን ስግብግብ ነጋዴዎችን የሚወሰደው ቁጥጥር እንዲጠናክር አመልክተዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በበኩላቸው ህዝቡ ከአገልግሎት አሰጣጥ፣ከልማት ተደራሽነትና ከኑሮ ውድነት ጋር ያነሳው ሃሳብን በዕቅድ በመያዝ ምላሽ እንዲያገኙ ይደረጋል ብለዋል። የማህበረሰቡን ፍላጎት መሠረት ያደረገ የልማት ስራዎችም ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። የዋጋ ግሽበትን ለመቅረፍ ምርታማነትን ማሳደግና ስግብግብ ነጋዴዎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።      
በክፍለ ከተማው የእንስሳት እርባታ ለወጣቶች የስራ እድል ለመፍጠርና ለገበያ ማረጋጋት እያገዘ ነው
Jan 25, 2026 80
ሸገር ፤ጥር 17/2018 (ኢዜአ)፡- በሸገር ከተማ አስተዳደር ፉሪ ክፍለ ከተማ የእንስሳት እርባታ ለወጣቶች የስራ እድል ለመፍጠርና ለገበያ ማረጋጋት እያገዘ ነው። በፉሪ ክፍለ ከተማ ሙዳ ወረዳ የስራ እድል ከተፈጠረላቸው ወጣቶች መካከል ቱሬ ቦሩ አምስት ሆነው በወተት ልማት በመደራጀት ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ገልጿል። ለስራው ውጤታማነትም የመንግስት የመስሪያ ቦታ መስጠትና፣ የብድር አቅርቦት ማመቻቸት እንዲሁም የስልጠና አገልግሎት እንዳገዛቸው ተናግሯል። የወተት ልማት ስራው በማደጉም በቀን በአማካኝ እስከ 110 ሊትር ወተት ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ከማረጋገጥ አልፈው ለሌሎች የስራ እድል መፍጠራቸውን ጠቁመዋል።   ሌላው የዚሁ ወረዳ ወጣት ሂንሰርሙ ፍቃዱ በበኩሉ በወተት ልማት ማህበር ስድስት ሆነው በመደራጀት በጀመሩት ስራ በቀን ከ100 ሊትር በላይ ወተት ለገበያ እያቀረቡ ይገኛሉ። በገቢውም ራሳቸውን ከመለወጥ አልፈው ለሌሎች ሰዎችም የስራ እድል ተጠቃሚ ማድረጋቸውን ጠቁመዋል። በዚሁ የወተት ልማት ማህበር ተቀጥረው የስራ እድል ተጠቃሚ ከሆኑት ሰዎች መካከል አቶ ተስፋዬ ተረፈ እንዳሉት በማህበሩ ተቀጥረው ከሚያገኙት ወርሃዊ ደሞዝ በተጓዳኝ በዘመናዊ የእንስሳት እርባታ ልምድ እንዳገኙ ገልጸዋል።   በከተማ አስተዳደሩ የፉሪ ክፍለ ከተማ ግብርና ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ሞቱማ ጉተታ እንደተናገሩት በክፍለ ከተማው ግብርናን በማዘመን ምርታማነቱን ለማሳደግ በተሰጠው ትኩረት የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ማረጋገጥ ተችሏል።   ከዚህ በተጓዳኝ ስራ አጥ ወጣቶቹን በማደራጀት በተለያዩ የስራ መስክ ለማሰማራት በክላስተር ደረጃ 329፣ በቤተሰብ ደረጃ ደግሞ 378 ሼዶች መተላለፋቸውን ተናግረዋል። በዚህም በወተት ላሞች እርባታ፣በከብት ማድለብ፣ በዶሮ እርባታ፣ በንብ ማነብና በአሳ ምርት በርካታ ዜጎች ተደራጅተው የስራ እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል።   የስራ እድሉ ተጠቃሚዎችን ውጤታማ ለማድረግም የቦታ አቅርቦትና ከሲንቄ ባንክ ጋር በማስተሳሰር ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር መቅረቡን ጠቅሰዋል። ከዚህ ባለፈም የስልጠናና የባለሙያ ድጋፍና ክትትልም፣ የእንስሳት መኖ አቅርቦትና የገበያ ትስስር እንደተፈጠረላቸው አንስተዋል።   በፉሪ ክፍለ ከተማ የሙዳ ወረዳ የግብርና ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ነጌሶ ደሜ በበኩላቸው በወረዳው ስራ አጥነትን ለመቅረፍ ዜጎች በእንስሳት እርባታ ዘርፍ ተደራጅተው ውጤታማ እንዲሆኑ እየተሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም 128 ሼዶችን በማቅረብና የብድር አቅርቦትን በማመቻቸት ለወጣቶች የስራ እድል መፍጠር መቻሉን አስረድተዋል። የእስሳት እርባታው የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ገበያን ለማረጋጋት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል።
በክልሉ ለሰላም ግንባታ እና ለልማት ስራዎች የተሰጠው ትኩረት፣ ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
Jan 25, 2026 117
ባህር ዳር፤ ጥር 17/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ለሰላም ግንባታ እና ለልማት ስራዎች የተሰጠው ትኩረት፣ ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የክልሉ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ገለጸ። በ2018 በጀት ዓመት ስድስት ወራት በክልሉ ከዘርፉ ከ7 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ መገኘቱንም አስታውቋል። በኢትዮጵያ በከፍተኛ ትኩረት እየተሰራባቸው ከሚገኙትና ከአምስቱ የኢኮኖሚ ምሰሶዎች መካከል ቱሪዝም አንዱ ነው። የመደመር መንግስት በኢትዮጵያ ያለውን የቱሪዝም ሀብት በአግባቡ መለየት፣ ማልማትና መጠቀም ላይ ያሉ ክፍተቶችን ለመሙላት በገበታ ፕሮጀክቶች የተገበራቸው የቱሪዝም ልማቶች በዘርፉ ዕድገት ላይ ከፍተኛ መነቃቃት ፈጥረዋል። የአማራ ክልል ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ሃላፊ መልካሙ ጸጋዬ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ በክልሉ በመጣው የተረጋጋ ሰላም በርካታ የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች የቱሪዝም መስህቦችን ለመጎብኘት እንዲመጡ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። በክልሉ ሃይማኖታዊና ታሪካዊ የአደባባይ በዓላት ያለምንም የጸጥታ ችግር መከበራቸውን ጠቅሰው፣ ተቀዛቅዞ የቆየው የቱሪዝም ዘርፍ በእነዚህ በዓላት መነቃቃቱን አመልክተዋል። በመሆኑም በክልሉ ለሰላም ግንባታና ለልማት ስራዎች የተሰጠው ትኩረት፣ ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም ገልጸዋል። በ2018 በጀት ዓመት ስድስት ወራት 10 ነጥብ 2 ሚሊየን ቱሪስቶች የክልሉን የመስህብ ሥፍራዎች መጎብኘታቸውን አመልክተው፣ ከእነዚህ ውስጥ 24 ሺህ የሚሆኑት የውጭ ሀገራት ጎብኚዎች መሆናቸውን አስታውቀዋል። በዚህም የጥምቀት በዓልን ሳያካትት ከ7 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን አንስተዋል። በክልሉ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት፣ የፋሲል አብያተ መንግስታት ጥገና እና የሌሎች ቅርሶች ጥገና፣ ጥበቃና እንክብከቤ የቱሪስቶችን ቀልብ እየሳበ መምጣቱን አመልክተዋል። እንዲሁም ለጎብኚዎች እየተሰጠ ያለው ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት የቱሪስቶች የቆይታ ጊዜ ከፍ እንዲል ማድረጉን አብራርተዋል። ቀደም ሲል የነበረው አማካይ የቱሪስቶች የቆይታ ጊዜ ከሁለት እስከ ሦስት ቀናት እንደነበረ አንስተው፤ አሁን ላይ ወደ አምስት ቀናት ከፍ ማለቱን ገልጸዋል። በቀጣይም የተገኙ ውጤቶችን የበለጠ አጠናክሮ በማስቀጠል ክልሉ ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ ሆኖ እንዲዘልቅ የ25 ዓመት የልማት ዕቅድና የ5 ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ መዘጋጀቱን አመልከተዋል።
ከቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በተጨማሪ በንግድ ትርኢት እና ባዛርም ምርቶች እየቀረቡ ነው
Jan 24, 2026 92
ጅማ፤ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ከተማ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ከማስፋፋት ባለፈ በሚዘጋጁ የንግድ ትርኢት እና ባዛሮች ነዋሪው ምርትና ሸቀጦችን በአንድ ቦታ እንዲያገኝ እየተደረገ ነው። በጅማ ከተማ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት የተዘጋጀ 15ኛ ዙር የንግድ ትርኢት እና ባዛር የተከፈተ ሲሆን፤ በባዛሩ ላይ ከመላው ሀገሪቱ የተውጣጡ ከ200 በላይ ነጋዴዎችና አምራቾች ተሳትፈዋል። የጅማ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ነጂብ ከድር በዚሁ ወቅት፤ የከተማው ነዋሪ በርካታ የገበያ አማራጭ እንዲያገኝ እየተደረገ ነው።   ዛሬ በከተማው የተከፈተው የንግድ ትርኢት እና ባዛርም ነዋሪው በአንድ ስፍራ ምርት እና ሸቀጦችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ እድል መፍጠሩን አስረድተዋል። የጅማ ከተማ ንግድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ጉተማ ጊዲ በበኩላቸው፤ በከተማው የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት እና ህገ ወጥ ንግድን ለመከላከል አማራጭ ገበያ የማስፋት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። በተለይም በከተማው የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን በማስፋት ሻጭ እና ሸማቹን አንድ ላይ ማገናኘት መቻሉን ጠቅሰው፤ ይህም ህገ ወጥ ደላሎች የሚፈጥሩትን ሰው ሰራሽ ችግር ማስወገድ አስችሏል ብለዋል። ከቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በተጨማሪ በተለይ በዓላትና የተለያዩ ሁነቶችን መነሻ በማድረግ የንግድና ትርኢት ባዛሮች እንዲዘጋጁ እየተደረገ መሆኑንም አስረድተዋል።
የግብርና ልማት ኢንሼቲቮችን ለማሳካት ዘርፉን በሎጂስቲክ የመደገፍ ሥራ ይጠናከራል
Jan 24, 2026 87
ሞጆ፤ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል እየተተገበሩ ያሉ የግብርና ልማት ኢንሼቲቮችን ለማሳካት ዘርፉን በሎጂስቲክ የመደገፍ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ጌቱ ገመቹ ገለፁ። ቢሮው የክልሉን የግብርና ዘርፍ በሎጂስቲክስ ለመደገፍ የሚያግዙ 795 ሞተር ብስክሌቶችና 73 ተሽከርካሪዎችን ዛሬ ለተለያዩ ወረዳዎች አስረክቧል።   አቶ ጌቱ ገመቹ በርክክብ መርሐ-ግብሩ ላይ፤ የሞተር ብስክሌቶቹና ተሽከርካሪዎቹ በአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ አካባቢ የግብርና ልማትን ለማፋጠን የሚከናወኑ ሥራዎችን እንደሚያግዙ ገልጸዋል።   በክልሉ የግብርና ሴክተሩን ለማዘመንና ለማሻገር የተለያዩ የሰብል፣ የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም የእንስሳት መኖ ልማት ኢንሼቲቮች ተቀርጸው እየተተገበሩ መሆኑንም አብራርተዋል። ልማቱን ውጤታማ ለማድረግም ከምርት ማሳደጊያ ግብዓት አቅርቦት በተጨማሪ በሎጂስቲክስ ለማገዝ እየተሠራ ነው ብለዋል። የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ለአርሶአደሩ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ እየቀረበ መሆኑን እና በዚህም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየሠራን ነው ሲሉ ገልጸዋል።   የክልሉ መንግሥት የመስኖ ፕሮጀክቶችን ከማስፋፋት ባለፈ የውሃ መሳቢያ ሞተሮችን ለአርሶ አደሩ በማቅረብ የበጋ ስንዴን ጨምሮ የመስኖ ልማት በስፋት እንዲከናወን እያደረገ ይገኛል። በዚህም በዘላቂነት ከተረጂነት ለመውጣት በርብርብ እየተሰራ መሆኑንም አመልክተዋል።   የቢሮው ምክትልና የሰብል ልማት ዘርፍ ኃላፊ በሪሶ ፈይሳ በበኩላቸው፤ መንግሥት የክልሉን የግብርና ልማት ለማሻገር የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። ተሽከርካሪዎችና ሞተር ብስክሌቶቹ በአርሶአደሩና አርብቶአደሩ አካባቢ ላሉ 72 ወረዳዎችና ለሸገር ከተማ አስተዳደር መሰጠታቸውንም ገልጸዋል።
የኤ ኤም ጂ ኢንዱስትሪ ፓርክን ከኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር መስመር ጋር የሚያገናኘው የባቡር መስመር ግንባታ ከተያዘለት ጊዜ ቀድሞ ይጠናቀቃል
Jan 24, 2026 108
አዲስ አበባ፤ ጥር 16/2018(ኢዜአ)፦ የኤ ኤም ጂ ኢንዱስትሪ ፓርክን ከኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር መስመር የሚያገናኘው የባቡር መስመር ግንባታ ፕሮጀክት ከተያዘለት ጊዜ ቀድሞ ማጠናቀቅ የሚያስችል ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ኢትዮ-ጁቡቲ ትራንስፖርት አክሲዮን ማህበር ገለጸ፡፡ የባቡር መስመር ግንባታ ፕሮጀክቱ ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያውያን አቅም መከናወኑ በቀጣይ በዘርፉ ለሚከናወኑ ሥራዎች የተሻለ ልምድና አቅም መፍጠር የሚያስችል መሆኑም ተጠቅሷል፡፡ ኤ ኤም ጂ ኢንዱስትሪ ፓርክን ከዋናው ኢትዮ ጅቡቲ ባቡር መስመር ጋር የሚያገናኘው የሶስት ኪሎ ሜትር የባቡር መስመር ግንባታ በመስከረም 29 ቀን 2018 ዓ.ም መጀመሩ ይታወቃል፡፡ የባቡር መስመሩ መገንባት የባቡር መሰረተ ልማትን በማስፋፋት የተለያዩ የወጭና ገቢ ምርቶችን ለማጓጓዝ የጎላ አበርክቶ ይኖረዋል፡፡ በኢትዮ-ጁቡቲ ትራንስፖርት አክሲዮን ማህበር ባለሙያዎች አቅም የሚገነባው ይሄው የባቡር መስመር ግንባታ በስድስት ወራት ለማጠናቀቅ ዕቅድ ተይዞለታል፡፡   የፕሮጀክቱ ማናጀር ኢንጅነር ንግስት ሀይሉ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የባቡር መስመሩን ግንባታ ከተያዘለት ጊዜ ቀድሞ ማጠናቀቅ የሚያስችል እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው፡፡ ባለፉት ሶስት ወራት የባቡሩን ሀዲድ ለማንጠፍ የሚያስችሉ የጉድጓድ ሙሌት፣ የአፈር ቆረጣና ሙሌት እንዲሁም የማፋሰሻ ግንባታዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የባቡር መስመር ግንባታው 70 በመቶ መድረሱን ገልጸው፤ ግንባታውን በአጭር ጊዜ ማጠናቀቅ የሚያስችል አፈጻጸም ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡ የባቡር መስመር ግንባታው በኢትዮጵያውያን አቅም የሚሰራ መሆኑን ገልጸው፤ አስፈላጊውን የሰው ሀይልና የግንባታ ግብዓቶች በማሟላት በትጋት እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ ግንባታው በኢትዮጵያውያን አቅም መሰራቱ በቀጣይ በዘርፉ ለሚከናወኑ ሥራዎች የተሻለ የሥራ ልምድና አቅም መፍጠር የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ገበያ ተኮር የግብርና ምርቶችን በብዛት የማምራት ሥራ እየተከናወነ ነው
Jan 24, 2026 103
አዳማ፤ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በገበያ ተፈላጊ የሆኑ የግብርና ምርቶችን በጥራት እና በብዛት የማምራት ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ ተናገሩ። በክልሉ የግብርና ሽግግር ሂደቱን ውጤታማ ለማድረግ ያለመ የሁለተኛ ምዕራፍ የትግበራ ፕሮግራም ለባለድርሻ አካላት የማስተዋወቂያ መድረክ በአዳማ ከተማ ተካሂዷል።   አቶ አወሉ በመድረኩ ላይ እንደገለፁት፤ የግብርና ዘርፉን ለማዘመን የተቀናጀ ቴክኖሎጂና ኤክስቴንሽን አገልግሎት ለአርሶአደሩ በአግባቡ ተደራሽ እየተደረገ ነው። ሁለተኛው ምዕራፍ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ትግበራ ፕሮግራም በተለይም አርሶአደሩ የቴክኖሎጂና የግብዓት አቅርቦት በሚፈልገው መልኩ እንዲያገኝ የሚያግዝ ነው ብለዋል። የአፈር ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘር፣ የእርሻ ትራክተርና ኮምባይነር በአግባቡ ማቅረብ እንዲቻል ሥራውን የሚያሳልጥ ኩባንያ እንደሚቋቋምም አመላክተዋል። በብዛት ከማምረትና በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ገበያ ተኮር የግብርና ምርቶች በማምረት ለውጪ ገበያ የማቅረብ ሥራው እንደሚጠናከር አስገንዝበዋል። አርሶ አደሩን ጨምሮ የግብርና ዘርፍ ባለድርሻ አካላት በገበያ ተፈላጊ የሆኑ ምርቶችን በጥራት፣ በብዛትና በአይነት ማምረት ላይ ማተኮር እንዳለባቸውም ነው ያስገነዘቡት። በግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ዳይሬክተር ደሳለኝ ዱጉማ በበኩላቸው፤ በክልሉ በ25 የግብርና የምርት አይነቶች ምርታማነት ለመጨመር ኢንሼቲቭ ተቀርጾ እየተሠራ ነው ብለዋል። ምርትና ምርታማነት እያደገ መምጣቱን ጠቅሰው፤ በክልሉ ከ7 ሚሊየን በላይ አርሶአደሮች በኩታ ገጠም ተደራጅተው ወጥነት ባለው መልኩ ቴክኖሎጂና የኤክስቴንሽን አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን ተናግረዋል። በተለይ በቴክኖሎጂ የተደገፈ ኢንዱስትሪ መር የግብርና አሰራርና አመራረት ሂደት ለመከተል እንዲሁም የአርሶአደሩን ተጠቃሚነትና የግብርና ሽግግር ለማፋጠን በትኩረት ሊሰራ ይገባል ብለዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት በተከናወነ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ፕሮግራም የሰብል እንዲሁም የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች ማሳደግ እንደተቻለም ጠቁመዋል። በዋና ዋና ሰብሎች በተለይ ስንዴ፣ የቢራ ገብስ፣ በቆሎና ሌሎች ሰብሎች ምርት ከመጨመር ባለፈ ከውጭ ሲገባ የነበረውን የስንዴና ቢራ ገብስ ምርት በሀገር ውስጥ መተካት መቻሉንም አስታውሰዋል። በሁለተኛው ምዕራፍ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ትግበራም ገበያ ተኮር የሰብል እና የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች በጥራት፣ በብዛትና በአይነት በማምረት በእሴት ሰንሰለት አልፈው ለገበያ እንዲቀርቡ ይደረጋል ብለዋል። በተጨማሪም የምርት ማቀነባበሪያዎች በማስፋፋት ረገድ አርሶ አደሩ ባለቤት እንዲሆንና ለምርቱ ተገቢውን ገበያ እንዲያገኝ የሚያስችል መሆኑንም አመላክተዋል።
የሴፍትኔት ፕሮግራሙ ከራስ አልፎ ለሌሎች መትረፍ የሚቻልበትን ዕድል ፈጥሯል
Jan 24, 2026 70
አዳማ፣ ጥር 16/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት ሶስት ዓመታት ሲተገበር የቆየው የምግብ ዋስትናና የሴፍትኔት ፕሮግራም ዜጎች ከራስ አልፈው ለሌሎች የሥራ ዕድል እንዲፈጥሩ ማስቻሉን የአዳማ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ። በአስተዳደሩ በምግብ ዋስትናና ልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም በመሳተፍ ሽግግር ያደረጉ 646 አባወራና እማወራዎች የምረቃ ሥነ-ሥርዓት ተካሂዷል።   የአዳማ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ንጋቱ ሞቱማ በዚሁ ወቅት፤ የከተሞች ልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም ድህነትን በመቀነስና የዜጎችን ኑሮ በማሻሻል በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ አበርክቷል ብለዋል። የፕሮግራሙ ተሳታፊዎች ባለፉት ሦስት ዓመታት በከተማ ጽዳትና ውበት፣ በአረንጓዴ ልማትና አካባቢ ጥበቃ ላይ በመሳተፍ የራሳቸውን ገቢ በመፍጠር ኑሯቸውን አሻሽለዋል ሲሉም ገልጸዋል። ፕሮግራሙ በከተማዋ በድህነት ውስጥ ያሉ ዜጎችን ኑሮ በመቀየር ረገድ ሚናው የጎላ መሆኑን ጠቅሰው፤ አስተዳደሩ ተጠቃሚዎቹን ወደ ዘላቂ ልማት በማሸጋገር ረገድ ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል። አስተዳደሩ ለሥራ እድል ፈጠራ የገነባቸውን ሼዶች የፕሮግራሙ ተሳታፊዎችን በማደራጀት አንደሚያስተላልፍና የባንክ ብድር የሚያገኙበትን ዕድል አንደሚፈጥርምአመልክተዋል።   የአዳማ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ሀብታሙ ግዛው በበኩላቸው፤ በከተማዋ በተመረጡ አካባቢዎች የልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራሙ መተግበሩን አውስተዋል። የፕሮግራሙ ተጠቃሚዎች ከጊዜያዊ ድጋፍ ባለፈ ከተረጅነት ራሳቸውን በማላቀቅ ቋሚ ጥሪት ማፍራት እንዲችሉ የመቋቋሚያ ድጋፍ እንደተደረገላቸውም አረጋግጠዋል።   ከተጠቃሚዎች መካከል የመልካ-አዳማ ወረዳ ነዋሪ ዓባይነሽ ደርቤ፣ በፕሮግራሙ ከመታቀፋቸው በፊት ከአራት ልጆቻቸው ጋር በችግር ውስጥ ይኖሩ እንደነበር ተናግረዋል። በከተማ ጽዳትና ውበት ስራ በመሳተፍ ከሚያገኙት ገቢ ቆጥበው የወተት ላም በመግዛት በአጭር ጊዜ ውስጥ ጥሪት ማፍራትና ኑሯቸውን ማሻሻል መቻላቸውንም ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም