ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በክልሉ የተሻሻለው የገጠር መሬት አዋጅ ዘመናዊ አሰራርን ለመከተልና የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ፋይዳው የላቀ ነው
Jan 12, 2026 43
ባህርዳር፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የተሻሻለው የገጠር መሬት አስተዳደር አዋጅ ዘመናዊ አሰራርን ለመከተልና የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ፋይዳው የላቀ መሆኑን የክልሉ መሬት ቢሮ ገለጸ። የቢሮ ኃላፊው ሲሳይ ዳምጤ፤ የተሻሻለውን የገጠር መሬት አስተዳደር አስፈላጊነትና ጠቀሜታ በተመለከተ መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም የተሻሻለው አዋጅ የገጠር መሬት ምዝገባ መረጃ ጥራቱን በጠበቀ አግባብ እንዲደራጅ ለማድረግና ለተጠቃሚ አርሶ አደሮች በአግባቡ ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም ዘመናዊ የመሬት አያያዝ ስርዓትን ለመዘርጋት እንደሚያስችል ገልጸዋል። አዋጁ አርሶ አደሩ የእርሻ መሬቱን ለልጆቹና ለስጋ ዘመዶቹ በውርስና በስጦታ እንዲያስተላልፍ መብት የሰጠ መሆኑን አንስተው በጋራ የመንገድ፣ የመብራት፣ የቴሌኮምና የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ለማድረግ ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል ብለዋል። አርሶ አደሩ ከአበዳሪ ተቋማት ብድር መውሰድ የሚያስችል እንዲሁም ዘመናዊ አሰራርን ተግባራዊ ለማድረግና የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ፋይዳው የላቀ መሆኑንም ገልጸዋል። በአዋጁ መሰረት አርሶ አደሩ መሬትን የመጠቀም መብት እንዳለው ሁሉ በአግባቡ ጠብቆና ተንከባክቦ ካልያዘ ደግሞ ከማስጠንቀቂያ ጀምሮ መሬቱን እስከመንጠቅ የሚደርስ እርምጃ እንዲወሰድ የሚያደርግ ስለመሆኑም አስረድተዋል። የግል፣ የመንግስትና የወል መሬትን ወሮ የተገኘ ከ30ሺህ ብር እስከ 100ሺህ ብር ወይም ከአንድ ዓመት እስከ አምስት ዓመት እስራት እንደሚቀጣ የሚደነግግ ሲሆን ሀሰተኛ የመሬት ማስረጃ ያቀረበም ከአንድ አመት እስከ ሶስት ዓመት በሚደርስ እስራት የሚቀጣ ይሆናል። የተሻሻለው የአማራ ክልል የገጠር መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም አዋጅ ባለፈው ወር አጋማሽ በተካሄደው የክልሉ ምክር ቤት 11ኛ መደበኛ ጉባኤ ፀድቆ ስራ ላይ መዋሉ ይታወቃል።
የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ የሚያጸኑ አስደማሚ የልማት ስኬቶች እየተመዘገቡ ነው
Jan 12, 2026 73
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በ2018 በጀት ዓመት ባለፉት ስድስት ወራት የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ የሚያጸኑ አስደማሚ የልማት ስኬቶች መመዝገባቸውን የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለጸ። የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት የበጀት ዓመቱን ያለፉት ስድስት ወራት የልማት አፈፃጸም አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥቷል። መግለጫውን የሰጡት የኢፌዴሪ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ኃላፊ ሚኒስትር እናትዓለም መለሰ፥ 2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ የማንሰራራት ዓመት ነው ብለዋል። በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራትም የኢትዮጵያን ማንሰራራት የሚያጸኑ አስደማሚ የልማት ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። በዚህም በብዝኅ የኢኮኖሚ ዘርፍ በ2030 ኢትዮጵያን አፍሪካዊት የብልጽግና ተምሳሌት የሚያደርጉ የልማት ስኬቶች እየተመዘገቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያም በሁሉም መስኮች ችግሮችን በማረም የኢትዮጵያን ዕድገት የሚያሳልጥ ውጤት መመዝገቡን አብራርተዋል። በዚህም በግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝምና ዲጂታል ብዝኅ የኢኮኖሚ መስኮች እመርታዊ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የመደመር መንግሥት እሳቤ በግብርና መስክ በበጋ መስኖ ስንዴ፣ በኩታ ገጠምና በሌማት ትሩፋት የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ተመጽዋችነትን የሚገታ የምርት ውጤት እየተገኘ መሆኑን አንስተዋል። የጉባ ብስራት ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅ ጠንካራ ክትትልና ድጋፍ እንደሚደረግ ጠቅሰዋል። ከተሞችን የብልጽግና ማዕከል ለማድረግ በአዲስ አበባ የተጀመረው የኮሪደርና የወንዝ ዳር ልማትም በበርካታ ከተሞች በስፋት እየተሰራበት መሆኑን ገልጸዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ምርቃት የጉባ ብስራት ፕሮጀክቶች ጅማሮም ኢትዮጵያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ጀምራ ማጠናቀቅ እንደምትችል የሚያሳዩ መሆናቸውን አብራርተዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ስኬትና የጉባ ብስራቶች ጅማሮ የመደመር መንግስት አካታችነትንና የኢትዮጵያን ዕድገት መሻት ለዓለም መድረክ የሚያረጋግጡ መሆናቸውን አብራርተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ግንባታው በይፋ የተጀመረው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያም የኢትዮጵያን ርዕይ የገለጠ የማንሰራራት ተምሳሌት ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ የኢትዮጵያና አፍሪካውያንን የአይችሉም ስብራት የደፈቀ ግዙፍ ፕሮጀክት ነው ያሉት ኃላፊዋ፤ ፕሮጀክቱም ኢትዮጵያን የወደፊቷ የአፍሪካና የዓለም ዋነኛ የአየር ትራንስፖርት በር ያደርጋታል ብለዋል። የዓለም አቀፍ አየር ማረፊው የአፍሪካውያንን ሁለንተናዊ ትስስር በማጠናከር አዳዲስ የኢኮኖሚ ዕድሎችን የሚያሰፋ ዘመናዊ የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሥርዓት የሚፈጥር መሆኑንም አስረድተዋል። በዲፕሎማሲ መስክም በሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን አሕጉራዊና ዓለም አቀፋዊ መድረኮች የኢትዮጵያ ተሳትፎም ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅ የአፍሪካ ድምጽ መሆን ያስቻለ ስኬት መመዝገቡን ተናግረዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የአፍሪካ ትርክትና ዕይታን የሚያንጸባርቅ አህጉራዊ ሚዲያ አስፈላጊነት በመገንዘብ ፐልስ ኦፍ አፍሪካ(POA) የተሰኘ ሚዲያ ማስጀመራቸውን አስታውሰዋል። ሚዲያው የአፍሪካን ድምፅና መሻት በማጉላት የአፍሪካውያንን ትስስርና አህጉራዊ ስኬቶች፣ ተግዳሮቶችንና ሕልሞችን በአፍሪካዊ ዕይታ ወደ መግለጥ መሸጋገሩን አብራርተዋል። በመንግስትና ሕዝብ መካከል የተደረጉ መድረኮችም ኢትዮጵያ ያስመዘገበችው የልማት ስኬት ዕውቅና የተሰጠበትና የህዝብና መንግስት መተማመን የተፈጠረበት መሆኑንም አብራርተዋል። በዚህ ዓመት የሚካሄዱት የሀገራዊ ምክክርና ሀገራዊ ምርጫ ዐበይትና ወሳኝ ሁነቶችን በአሳታፊነት፣ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ መንገድ በስኬት ለማስኬድም መንግስት በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
ከክልሉ ባለፉት ስድስት ወራት 33ሺህ 700 ቶን የቡና፣ ሻይ እና ቅመማቅመም ምርት ለማዕከላዊ ገበያ ቀርቧል
Jan 12, 2026 59
ቦንጋ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል 33ሺህ 700 ቶን የቡና፣ ሻይ እና ቅመማቅመም ምርት ለማዕከላዊ ገበያ መቅረቡ ተመለከተ። የክልሉ መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ሃላፊ የሺዋስ ዓለሙ፤ በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራትንና ቀጣይ አቅጣጫዎችን በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል። በተለይም በግብርናው ዘርፍ በዋና ዋና ሰብሎች እንዲሁም በቡና፣ ሻይ እና ቅመማቅመም ምርቶች ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተዋል። በዚህም መሰረት በክልሉ በዋና ዋና ሰብሎች 384 ሺህ ሄክታር መሬት በማልማት ከ20 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስድስት ወራት 33 ሺህ 700 ቶን የቡና፣ ሻይ እና ቅመማቅመም ምርት ለማዕከላዊ ገበያ መቅረቡን ጠቁመው ከቀረበው ውስጥ 13ሺህ ቶኑ ቡና፣ 2ሺህ 700 ቶኑ ሻይ እና 18 ሺህ ቶኑ ቅመማቅመም መሆኑን አመልክተዋል። በሌላ በኩል በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት ከ255 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ መቅረቡንም ጠቁመዋል። በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ አገልግሎትና ሌሎች ዘርፎች ለተሰማሩ 52 ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፍቃድ መሰጠቱን ገልጸዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርም በርካቶች ተሰማርተው ስኬታማ መሆናቸውንና ለሌሎችም ጭምር የስራ ዕድል መፍጠራቸውን አንስተዋል። የውሃ፣ የመስኖ፣ የመንገድና ድልድዮችን፣ እንዲሁም የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረጉ መሰረተ ልማቶች መከናወናቸውን ተናግረዋል። በተለይም በከተሞች ፈጣንና ቀልጣፋ የዲጂታል አገልግሎት በመስጠት በኩል መልካም ጅምሮች መኖራቸውን አንስተው በተጠናከረ መልኩ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በክልሉ ሕገ ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን በመከላከል ገበያን የማረጋጋት ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jan 12, 2026 87
ሚዛን አማን፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ባለፉት ስድስት ወራት ሕገ ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን በመከላከል ገበያን ለማረጋጋት የተሰራው ሥራ ውጤታማ በመሆኑ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ ገለጸ። የቢሮው ኃላፊ አቶ ታሪኩ አካሉ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ሕገወጥ ንግድና የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴ የገበያ ዋጋን በማናር በዜጎችና በሀገር ላይ ጉዳት ያደርሳል። ይህን ለማስቅረትም በክልሉ በህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድ እንቅስቃሴ ላይ የሚሳተፉ አካላትን ተከታትሎ እርምጃ በመውሰድ የመከላከል ሥራ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ ስድስት ወራት በምርቶች ላይ ምክንያታዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ ባደረጉና በሕገ ወጥ የነዳጅ ግብይትና መሰል ተግባራት ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎችን በመከታተል እርምጃ መወሰዱን ተናግረዋል። እንደኃላፊው ገለጻ፤ በገንዘብ ከተቀጡት ነጋዴዎች መካከል 1ሺህ 670 የሚሆኑት ለመንግስት ሠራተኞች የተደረገን የደመወዝ ማሻሻያን ተከትሎ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በማድረጋቸው እርምጃ የተወሰደባቸው ናቸው። በቀጣይም የተጋነነ የዋጋ ጭማሪና የምርት ስወራ እንዳይኖር በመከላከል ገበያን ለማረጋጋት የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አመልክተዋል። ባለፉት ስድስት ወራት ገበያን ለማረጋጋት የተሰሩ ሥራዎች ውጤታማ መሆናቸውን የገለጹት ሃላፊው፣ ህጋዊ የግብይት ስርዓቱን ለማጠናከርም ግብ ተይዞ እየተሰራ መሆኑንም አስረድተዋል። ከሚዛን አማን ከተማ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ወይንሸት ዘውዴ፤ መንግሥት በንግድ እንቅስቃሴው ላይ የሚፈጸሙ ህገወጥ ተግባራትን ለመቆጣጠር እያከናወናቸው ያሉ ተግባራት ለሸማቹ መብት መከበር ያለው ሚና ከፍተኛ በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል። አንዳንድ ነጋዴዎች በሕገ ወጥ መንገድ ለመክበር የሚያደርጉት ጥረት ሕዝብና ሀገር ላይ ከፍተኛ ጫና እንደሚፈጥር ገልጸው፣ በመንግስት ህገወጥነትን ለመከላከል ለሚሰሩ ሥራዎች በአቅማቸው ለመደገፍ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።
በአፋር ክልል ባለፉት ስድስት ወራት ከ3 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰበሰበ
Jan 12, 2026 58
ሰመራ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት ከ3 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኀላፊ አቶ አወል አብዱ፤ የበጀት ዓመቱን የስድስት ወራት የገቢ አሰበሰብ ሂደቱን አስመልክተው ዛሬ መግለጫ ሰጥተዋል። አቶ አወል በመግለጫቸው፤በበጀት ዓመቱ በስድስት ወራት ውስጥ 4 ቢሊዮን 78 ሚሊዮን 630 ሺህ ለመሰብሰብ ታቅዶ 3 ቢሊየን 998 ሚሊዮን 779 ሺህ ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። ገቢው የተሰበሰበው ቀጥታና ቀጥታ ካልሆኑ ታክሶችና ከሌሎች የገቢ አርዕስቶች መሆናቸውንም ገልጸዋል። በግብር አሰባሰቡ የእቅዱን 98 በመቶ ማከናወን መቻሉን ገልፀው በቀጣይም የገቢ አሰባበሰብ ሂደቱን በማዘመን የክልሉን ልማት ለማሳካት ርብርብ እንደሚደረግ ተናግረዋል። የገቢ አፈጻጸሙ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር በ1 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር በላይ ብልጫና የ50 በመቶ ዕድገት ማሳየቱን ሃላፊው አስረድተዋል። በክልሉ ገቢን አሟጦ ለመሰብሰብ የሚያስችል ከክልል እስከ ቀበሌ ድረስ በተሰሩ የንቅናቄና የግንዛቤ ማሳደግ ስራዎች ግብርን በጊዜ የመክፈል ሁኔታው እየተሻሻለ መምጣቱን ገልፀዋል። በተለይም የግብር አሰባሰቡን ዲጂታላይዝ በማድረግ ግብር ከፋዩ በቀላሉ መስተናገድ እንዲችል በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዘርፉ የተሻሉ አሰራሮችን በመዘርጋትና ህገ ወጥ ግለሰቦችን ወደ ህጋዊነት የማምጣት ስራዎች መሰራታቸውን ጠቁመው፤ ወደ ትክክለኛው መንገድ መምጣት ባልቻሉት ላይ ደግሞ ህጋዊ እርምጃ የሚወሰድ መሆኑንም አቶ አወል ገልጸዋል።
በመጀመሪያው መንፈቀ-ዓመት 4 ነጥብ 854 ሺህ ቶን የሻይ ልማት ምርት ተሰበሰበ
Jan 12, 2026 58
አዲስ አበባ፤ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፡-በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ በባለሃብትና በአርሶ አደር ከለማው የሻይ ልማት 4 ነጥብ 854 ሺህ ቶን ምርት መሰብሰቡን የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን አስታውቋል። በባለሃብትና በአርሶ አደር 6 ሺህ 396 ሔክታር በሻይ ልማት መሸፈኑን በባለሥልጣኑ የቡና፣ ሻይና ቅመማቅመም ልማት መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፍቃዱ ደፈረስ ለኢዜአ ተናግረዋል። በአጠቃላይ ከለማው ውስጥ አሁን ላይ ምርት የሚሰጠው 4 ሺህ 936 ሔክታር መሆኑንም ነው የተናገሩት። ከዚህም በተጠናቀቀው የበጀት ዓመቱ አጋማሽ 4 ነጥብ 854 ሺህ ቶን የሻይ ልማት ምርት መሰብሰቡን አረጋግጠዋል። እስካሁን ባለው መረጃና ልየታ መሠረት በኢትዮጵያ ለሻይ ቅጠል ልማት ተስማሚና ምቹ የሆነ ከ6 ሚሊየን ሔክታር የሚልቅ መሬት መኖሩን አመላክተዋል። ካለው የመልማት ዐቅም አንጻር እየለማ ያለው አነስተኛ መሆኑን አንስተው፤ በዘርፉ በቀጣይ የተሻለ ለመሥራት መንግሥት ትኩረት መስጠቱን አስታውቀዋል። ኢትዮጵያ የሻይ ቅጠል ወደ ተለያዩ ሀገራት በመላክ የውጭ ምንዛሪ ፍላጎቷን እንደምትደጉምም አንስተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በአስተዳደሩ በምግብ ዋስትናና በልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም የታቀፉ ወገኖች ኑሮ እንዲሻሻል የሚደረገው ድጋፍ ይጠናከራል
Jan 11, 2026 136
አምቦ፤ጥር 3/2018 (ኢዜአ)፦የአምቦ ከተማ አስተዳደር በምግብ ዋስትናና በልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም የታቀፉ ወገኖች ኑሮ ይበልጥ እንዲሻሻል ድጋፉ እንደሚጠናከር የአስተዳደሩ ከንቲባ ሃጫሉ ገመቹ ገለጹ። በአምቦ ከተማ በሁለተኛ ዙር የምግብ ዋስትናና ልማታዊ ሴፍቲኔት የኑሮ ማሻሻያ ፕሮግራም በመሳተፍ ሽግግር ያደረጉ 1ሺህ 176 ተጠቃሚዎች ዛሬ ተመርቀዋል። በምረቃ ሥነ ሥርአቱ ላይ የተገኙት የአምቦ ከተማ ከንቲባ አቶ ሃጫሉ ገመቹ፣ ከዚህ ቀደም የህብረተሰቡ የሥራ ባህል አለመጎልበት ጋር ተያይዞ ሰርቶ ለመለወጥና ልማትን ለማፋጠን ተጽዕኖ ሲያደርግ ቆይቷል። ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ህብረተሰቡ በልማት ሥራዎች በንቃት እንዲሳተፍ መደረጉ ተጠቃሚነቱን ከማሳደግ ባለፈ የሥራ ባህሉን እየቀየረው መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም ሰርቶ በመለወጥ የራሱን ኑሮ ከመምራት ባለፈ በሃገራዊ እድገት ውስጥ የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን አመልክተዋል። በተለይም የልማታዊ ሴፍቲኔት የኑሮ ማሻሻያ ፕሮግራም ተግባራዊ ከሆነ በኋላ የፕሮግራሙ ተሳታፊዎች የጊዜ አጠቃቀምና የቁጠባ ባህል ማደጉን ነው የጠቆሙት። በከተማዋ የህብረተሰቡን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የተለያዩ ኢንሼቲቾች መተግበራቸውንም ከንቲባ ሃጫሉ ጠቅሰዋል። ህብረተሰቡን ከተረጂነትና ጠባቂነት ለማላቀቅ የተጀመሩ ኢኖሼቲቮች እንደሚቀጥሉ ገልጸው፣ በተለይ በምግብ ዋስትናና በልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም የታቀፉ ወገኖች ኑሮ ይበልጥ እንዲሻሻል አስተዳደሩ የሚያደርገውን ድጋፍ ያጠናክራል ብለዋል። የአምቦ ከተማ አስተዳደር የምግብ ዋስትና እና የልማታዊ ሴፍቲኔት የኑሮ ማሻሻያ ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ ተስፋዬ ድሪርሳ በበኩላቸው፣ ከተረጂነት ለመውጣት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በፕሮግራሙ ታቅፈው ውጤታማ በመሆን የተሸጋገሩና ዛሬ ለምረቃ የበቁ ወገኖች በከተማ ግብርና፣ በፅዳት፣ውበትና በተፋሰስ ልማት ስራዎች ተሰማርተው ሲሰሩ የቆዩ መሆናቸውን ገልጾዋል፡፡ በሁለተኛ ዙር የምግብ ዋስትናና ልማታዊ ሴፍቲኔት የኑሮ ማሻሻያ ፕሮግራም ተሳትፈው የተመረቁት ወገኖች ወደፊት ሥራቸውን በውጤታማነት አጠናክረው እንዲቀጥሉ 77 ሚሊዮን 616 ሺህ ብር በድጋፍ መሰጠቱንም ተናግረዋል፡፡ ዜጎች በፕሮግራሙ መታቀፋቸው ሰርተው ለመለወጥ ከማስቻሉ ጎን ለጎን የቁጠባ ባህላቸውን እንዲያሳድጉና በከተማዋ የልማት ሥራዎች ላይ የድርሻቸውን እንዲወጡ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡ በፕሮግራሙ ታቅፈው ውጤታማ ከሆኑት መካከል በከተማው የያእ ገዳ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ተረፈ ሙለታ በልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም ከመታቀፋቸው በፊት በችግር ውስጥ ይኖሩ እንደነበር አስታውሰዋል። በፕሮግራሙ ከታቀፉ በኋላ የጀመሩት ሥራ ውጤታማ በመሆኑ በአሁኑ ወቅት ካፒታላቸውን በማሳደግ ወደ ከብት ማድለብ ሥራ መሸጋገራቸውን ተናግረዋል፡፡ በተለያዩ ጊዜያት በባለሙያዎች የተለያዩ ስልጠናዎችን ማግኘታቸው በስራቸው ውጤታማ ለመሆን እንዳገዛቸው የተናገሩት ደግሞ ሌላው ነዋሪ ወይዘሮ ብርቄ ባሊ ናቸው። ሰርተው ከሚያገኙት ገቢ የቁጠባ ባህላቸው ማደጉንም ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት በተሰማሩበት የዶሮ እና የበግ እርባታ ሥራ ውጤት በማስመዝገብ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን እያስተዳደሩ መሆናቸውንም ገልጸዋል።
በአፋር ክልል ከለውጡ ዓመታት ወዲህ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የክልሉን የመልማት አቅምን ያሳዩ ናቸው
Jan 11, 2026 202
ሰመራ፣ጥር 3/2018(ኢዜአ)፦በአፋር ክልል ከለውጡ ዓመታት ወዲህ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የክልሉን የመልማት አቅም ማሳየት የቻሉ መሆናቸውን በብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ ኀላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ ተናገሩ። በብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ አመራሮች በክልሉ በሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደርና በዱብቲ ወረዳ እየተሰሩ ያሉ የልማት ስራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። በብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ ኀላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ በወቅቱ እንዳሉት፥ በአፋር ክልል ከለውጡ ዓመታት ወዲህ በርካታ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል። የልማት ስራዎቹ የክልሉን የመልማት አቅም ያሳዩ መሆናቸውን አመልክተዋል። የአዋሽ ወንዝን ለመስኖ አገልግሎት እንዲውል በማድረግ ሰፋፊ እርሻዎች መሠራታቸውን መመልከታቸውን ገልጸው፤ በተለይም በዱብቲ ወረዳ እየለማ ያለው የስንዴና የሱፍ ምርት አስደናቂ መሆኑን ተናግረዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃግብር በተለይም በዶሮ፣እንቁላል፣ በዘመናዊ ከብት እርባታ ረገድ እየተሰሩ ያሉ ስራዎችም የሚበረታቱ መሆናቸውን ገልፀዋል። ክልሉ የብልፅግና ተስፋ የሚታይበት መሆኑን የገለፁት አቶ ፍቃዱ፤በሠመራ ከተማ እየተሰራ ያለው የኮሪደር ልማትም የህብረተሰቡን ባህልና እሴት መሠረት ያደረገ፣ከተሜነትን ያዋሃደና ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያለው መሆኑን ገልፀዋል። በብልፅግና ፓርቲ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ምክትል ኀላፊ ወይዘሮ ማርታ ወይቤ በበኩላቸው፥ በክልሉ የተሰሩ ስራዎች ከዚህ ቀደም ስለ በረሃ የነበረውን አመለካከት ጭምር የቀየሩ ናቸው ብለዋል። በተለይም የሠመራ ከተማ ኮሪደር ልማት ባህላዊ ይዘቱን የጠበቀ፣ማራኪና ከተማዋን እያንሰራሩ ከሚገኙ ከተሞች ተርታ እንድትመደብ የሚያደርጋት መሆኑን አመልክተዋል። በክልሉ በለውጡ ዓመታት የታዩ ተግባራት የሀገሪቷን ማንሰራራትና እመርታዎችን ያንፀባረቁ መሆናቸውን ተናግረዋል። በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኀላፊ አቶ አብርሃም ታደሰ በበኩላቸው፥ በአፋር ክልል ሀብትን በአግባቡ በመጠቀም የብልፅግናን መንገድ የሚያግዙ ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን ተናግረዋል። የህዝብ ተጠቃሚነትን መሠረት ያደረጉ ስራዎች በተቀናጀና በተደራጀ መንገድ እየተሰሩ መሆናቸውን ተመልክተናል ብለዋል። "ጠንካራ አደረጃጀት ለጠንካራ ፓርቲ" በሚል መሪ ሀሳብ በብልፅግና ፓርቲ ዋና ፅህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ የ2018 የ6 ወራት አፈፃፀም ግምገማና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ መድረክ ትናንት በሰመራ ከተማ መካሄዱ ይታወሳል።
የኢትዮጵያን የከፍታ ጉዞ ለማረጋገጥ የባህር በር ወሳኝ ነው-የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች
Jan 11, 2026 98
አዲስ አበባ፣ጥር 3/2018(ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያን የከፍታ ጉዞ ለማረጋገጥ የባህር በር ማግኘት ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አባላት ገለጹ። የኢትዮጵያ የባህር በር ማጣት የመላው ኢትዮጵያውያንን ልብ ያደማ የማይረሳ ጠባሳ መሆኑን አመራር አባላቱ ተናግረዋል፡፡ የባህር በር ባለቤትነት የረጅም ዓመታት ስትራቴጂካዊ ዕቅድን፣የትውልድንና የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅምና ከፍታ ለማረጋገጥ ያለመ መሆኑንም ጠቁመዋል። ጉዳዩን ለዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ለማስገንዘብ የተጀመሩ የዲፕሎማሲ ሥራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አባላት ጠቅሰዋል፡፡ የአገው ለፍትህና ለዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ሰብሳቢ አዲሱ መኮንን (ዶ/ር)፥ ኢትዮጵያ በፖለቲካ ሴራ የባህር በር ያጣችበት ሂደት የሚያስቆጭ መሆኑን ገልጸዋል። የባህር በር ለአገር እድገት የጀርባ አጥንት መሆኑን አንስተው፤ኢትዮጵያ የባህር በር ማጣቷ በኢኮኖሚ ዕድገቷ ላይ ከፍተኛ ተግዳሮት መፍጠሩን ተናግረዋል። የባህር በር ባለቤትነትን ለማረጋገጥ ሁሉም ኢትዮጵያዊ ለስኬቱ በጋራ እየተረባረበ መሆኑን አመልክተዋል። የራያ ራዩማ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ የውጭ ግንኙነት ኃላፊ ጌታቸው ከበደ በበኩላቸው እንደገለጹት፤የኢትዮጵያን የከፍታ ጉዞ ለማረጋገጥ የባህር በር ማግኘት ዋነኛ መሰረት ነው ብለዋል፡፡ የባህር በር ጉዳይን ዓለም አቀፍ አጀንዳ በማድረግ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የሚደነቁና የሚደገፉ መሆናቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት እያደገ የመጣውን የኢትዮጵያ ህዝብ እና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለማስተናገድ የባህር በር ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ ፓርቲ (ኢዜማ) የብሔራዊ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አሰፉ ተረፈ በበኩላቸው፤ የባህር በር ጉዳይ የሁላችንም ጥያቄ በመሆኑ በጋራ እንሰራለን ሲሉ አረጋግጠዋል። በዚህ ረገድ መንግስት የጀመረው ጥረት ግቡን እንዲመታ የሁሉም ኢትዮጵያውያን ሚና ወሳኝ መሆኑንም አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ አንድነት ፓርቲ ሊቀ መንበር ዘሪሁን ገብረእግዚአብሄር፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ማጣት የኢትዮጵያውያንን ልብ በእጅጉ ያደማ የታሪክ ጠባሳ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ የራሷን የባህር በር ያጣችበት ሂደት ኢ-ፍትሃዊ መሆኑን አንስተው፥ አሁን ላይ ጉዳዩ ብሔራዊ አጀንዳ ሆኖ ሁሉም የበኩሉን ማድረጉ የሚደነቅ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የትውልዱ አጀንዳ ነው
Jan 11, 2026 109
ሀዋሳ፤ጥር 3/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የትውልዱ አጀንዳ ሆኖ የሚቀጥልና የሀገር የህልውና ጉዳይ መሆኑን የተለያዩ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ገለጹ፡፡ ለብዙ ዘመናት የባህር በር ባለቤት የነበረችው ኢትዮጵያ ምክንያቱ በግልጽ በማይታወቅ መልኩ ለዓመታት የባህር መግቢያና መውጫ የተቆለፈባት ሀገር ሆናለች። በአሁኑ ወቅት ከ120 ሚሊዮን በላይ የሚገመት ህዝብ ላላት ሀገር የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከገቢና ወጪ ንግድ ባለፈ የሀገርን ህልውና የሚወስን የትውልድ ጥያቄም ጭምር ሆኖ በስፋት እየተነሳ ይገኛል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የትውልዱ አጀንዳ ሆኖ የሚቀጥል የሀገር ህልውና ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። የሲዳማ አርነት ንቅናቄ የፓርቲ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል አቶ ደምሴ ሱካሬ፤ ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችበት ሁኔታ ለህዝብ ግልጽ ያልሆነና ቁጭት ፈጥሮ የቆየ ጉዳይ መሆኑን አስታውሰዋል። የነበራትን የባህር በር አጥታ በዝምታ ዓመታት አልፈው በአሁኑ ወቅት ትውልዱ ጥያቄውን በይፋ እያነሳና ተገቢ ምላሽ የሚጠብቅ ሀገራዊ አጀንዳ እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል። በመሆኑም የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከምጣኔ ሀብት፣ከፖለቲካ፣ ከዲፕሎማሲና ቀጣናዊ የልማት ትስስር ባለፈ ብሔራዊ ደህንነት ጉዳይ በመሆኑ ምላሽ ሊሰጠው ግድ ይላል ብለዋል። በኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅምና በህልውናዋ ጉዳይ በተቃራኒ ሊቆም የሚችል ዜጋ መኖር እንደሌለበት አንስተው፥ ፓርቲያቸው በዚህ ረገድ የጸና አቋም ያለው መሆኑን አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ሶሻል ዴሞክራቲክ ፓርቲ የድርጅት ጉዳይ ዘርፍ ኃላፊ በለጠ ሲጌቦ፤ የባህር በር ጉዳይ በአደባባይ ከመነሳቱ ባለፈ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ጭምር እንዲገነዘበው መደረጉ ትልቅ የዲፕሎማሲ ስኬት መሆኑን ገልጸዋል። ጥያቄው ተገቢ ምላሽ እስከሚያገኝ ድረስ የትውልዱ ጥያቄ በተጠናከረ መልኩ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በብልጽግና ፓርቲ የሲዳማ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ ተስፋዬ ኤርሚያስ፤ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የሀገር ህልውና ጉዳይ በመሆኑ ምላሽ እንዲያገኝ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቱ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። የባህር በር ጥያቄ ለኢትዮጵያ የቅንጦት ሳይሆን እያደገ የመጣውን ህዝቧን ለመመገብ፣ በዓለም አቀፍ መድረክ ተወዳዳሪ ለመሆንና ብሔራዊ ደህንነቷን ለማስጠበቅ ጭምር መሰረታዊ ጉዳይ በመሆኑ ምላሽ ሊያገኝ ግድ ይላል ብለዋል። ኢትዮጵያ የባህር በር ተቆልፎባት መኖር የማትችል መሆኑን ዓለም እንዲገነዘበው መደረጉን አንስተው፥ ምላሽ እስከሚያገኝ ድረስ ጥረቱ ይቀጥላል ሲሉ አረጋግጠዋል።
በክልሉ የተለያዩ ከተሞች 100 ኪሎ ሜትር የሚጠጋ የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ ነው
Jan 11, 2026 110
ባህር ዳር፤ ጥር 3/2018(ኢዜአ):-በአማራ ክልል በተለያዩ ከተሞች 100 ኪሎ ሜትር የሚጠጋ የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ የክልሉ ከተሞችና መሰረተ ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው አማካሪ አቶ ሽቤ ክንዴ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የኮሪደር ልማት ሥራው የከተሞችን ገፅታ ከመቀየር ባለፈ ለኑሮ ምቹና ተወዳዳሪነታቸው ከፍ እንዲል እያደረገ ነው። ባለፉት ጊዜያት የተገኙ ተሞክሮዎችን በማስፋት በዚህ ዓመት በስምንት ዋና ዋና ከተሞችና በ20 መካከለኛና አነስተኛ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። እስካሁን በተደረገ ጥረትም ከ24 ነጥብ 6 ኪሎ ሜትር በላይ የአስፋልት መንገድን ጨምሮ የእግረኛ፣ የብስክሌትና ሌሎችን መሰረተልማቶችን ያካተተ የኮሪደር ልማት ለማከናወን ተችሏል። በተጨማሪም በከተሞች ልማቱ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች፣ የአረንጓዴ ቦታዎች፣ የህፃናት መጫዎቻ፣ አደባባዮችና ሌሎች የመዝናኛ ስፍራዎችን አካቶ እየተከናወነ መሆኑን ነው ያስታወቁት። ለልማት ስራው ከ4 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 1ነጥብ 8 ቢሊዮን የሚሆነው ከህብረተሰቡ በድጋፍ የተገኘ መሆኑን አንስተዋል። በልማት ሥራው አንድ ሚሊዮን ለሚጠጉ ወገኖች የሥራ እድል በመፍጠር በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለም ጠቁመዋል። በባህር ዳር ከተማ ሦስተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ሥራ መጀመሩን እና በሌሎች ዋና ዋና ከተሞችም አንደኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ሥራ ተጠናቆ ሁለተኛው ምዕራፍ እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። የኮሪደር ልማት ሥራው ቀደም ሲል በልማት ወደኋላ ቀርተው የነበሩ ከተሞችን ደረጃቸውን በጠበቀ አግባብ እንዲገነቡ ለማድረግ ማስቻሉንም አስገንዝበዋል። ለአረንጓዴ ቦታና ለመዝናኛ ስፍራ ትኩረት ሰጥቶ እየተከናወነ በመሆኑ የከተሞች ገጽታ እየተቀየረ መምጣቱንም ተናግረዋል። ከተሞች በፕላን እንዲመሩ፣ ለኑሮ የተመቹ እንዲሆኑ እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችን በማሳለጥ የቱሪዝም ሳቢነታቸውን በማሳደግ ብቁና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አስችሏል ብለዋል። የኮሪደር ልማት ሥራው በጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር እየተመራ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ ልማቱ የህብረተሰቡን የሥራ ባህል በማዳበር ኑሮውን በማሻሻል ረገድ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም አንስተዋል። በቀሪ ወራትም ዕቅዱን በተሟላ መንገድ ለማከናወን የአመራሩም ሆነ የባለሙያ እገዛ ይበልጥ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስገንዝበዋል። ልማቱን ወደ ሌሎች ከተሞች የማስፋት ሥራ እንደሚከናወን አንስተው፤ ለዚህም የዲዛይን፣ መሬትን ከሦስተኛ ወገን ነፃ የማድረግና ሃብት የማሰባሰብ ስራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። በክልሉ ባለፈው ዓመት በሰባት ከተሞች 35 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ በተሻለ ጥራትና ፍጥነት ማከናወን እንደተቻለም አቶ ሽቤ ጨምረው አስታውሰዋል።
በሀላባ ዞን የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ
Jan 11, 2026 200
ቁሊቶ፤ ጥር 3/2018 (ኢዜአ) ፡- በሀላባ ዞን የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል፡፡ በዞኑ አስተዳደርና በህብረተሰቡ ተሳትፎ ተሰርተው የተጠናቀቁ ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት የተደረጉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በተገኙበት ነው ፡፡ የሀላባ ስታዲየም የመጀመሪያ ምዕራፍ ፕሮጀክት ግንባታ፣ የዞን አስተዳደር ህንጻና በአንድ ከተማ የአንድ ፕሮጀክት ኢንሼቲቭ አካል የሆነው የማህበረሰብ መድሃኒት ቤትና ሌሎች የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ከተደረጉት መካከል ናቸው፡፡ ፕሮጀክቶቹ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን የተቀላጠፈ ለማድረግና ጤናማና አምራች ዜጎችን ለመፍጠር እየተደረገ ያለውን ጥረት ከማጠናከር በተጨማሪ የቁሊቶ ከተማን በኢኮኖሚ ተወዳዳሪ እንደሚያደርጉም ተገልጿል፡፡ ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቁት ፕሮጀክቶች የመንግስትንና የማህበረሰብን አቅም አስተባብሮ በመጠቀም የጋራ ተጠቃሚነትን እውን ማድረግ እንደሚቻል በተጨባጭ ተሞክሮ የተወሰደበት ስለመሆኑም ተጠቁሟል፡፡ የፕሮጀክቶቹ ምረቃ የተካሄደው የሀላባ ዘመን መለወጫ ‹‹ሴራ›› በዓል ከፌዴራል፣ ከክልልና ከተለያዩ መዋቅሮች የተገኙ ከፍተኛ አመራሮች፣ ተጋባዥ እንግዶችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በተገኙበት እየተከበረ ባለበት ወቅት ነው፡፡
በበጀት ዓመቱ አጋማሽ ከ15 ነጥብ 8 ሚሊየን ኩንታል በላይ ቡና ተመርቷል
Jan 11, 2026 111
አዲስ አበባ፤ ጥር 3/2018 (ኢዜአ)፡- በተያዘው በጀት ዓመት የመጀመሪያ አጋማሽ ከ15 ነጥብ 8 ሚሊዮን በላይ ኩንታል ቡና መመረቱን የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን አስታወቀ። በተያዘው ዓመት 2 ሚሊየን 462 ሺህ 718 ሔክታር በቡና ልማት መሸፈኑን በባለሥልጣኑ የቡና፣ ሻይና ቅመማቅመም ልማት መሪ ሥራ አስፈጻሚ ፈቃዱ ደፈረስ ለኢዜአ ተናግረዋል። ከዚህ ውስጥ አሁን ላይ ምርት የሚሰጥ የቡና መሬት ሽፋን በአርሶ አደር 1 ሚሊየን 537ሺህ 626 እንዲሁም በባለሃብት 143 ሺህ 140 ሔክታር መሆኑንም አስረድተዋል። በሌላ በኩል ዘንድሮ የለማው መሬት ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ20 ነጥብ 7 በመቶ እንዲሁም ካለፉት ሥድስት ዓመታት ጋር ሲነፃፀር የ211 በመቶ ብልጫ ማሳየቱን አረጋግጠዋል። በተጠናቀቀው ግማሽ የበጀት ዓመት ከ15 ነጥብ 8 ሚሊየን ኩንታል በላይ ቡና መመረቱን ጠቅሰው፤ ከዚህ ውስጥ 14 ነጥብ 37 ሚሊየን ኩንታል በአርሶ አደር ቀሪው በባለሃብት መመረቱን ገልጸዋል። ይህም ካለፉት ሥድስት ዓመታት ጋር ሲነፃፀር ከሦስት እጥፍ በላይ ብልጫ ማሳየቱን ነው ያስታወቁት። ምርታማነትን በተመለከተም በባለሃብት 9 ነጥብ 9 እንዲሁም በአርሶ አደር ማሳ 9 ነጥብ 4 ኩንታል በሔክታር መሆኑን ጠቅሰዋል። የቡና ምርታማነትንና ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እየተሠራ መሆኑን ገልጸው ባለፉት ሰባት ዓመታት ከ862 ሺህ ሔክታር በላይ ያረጁ ቡናዎች መታደሳቸውንና 9 ቢሊየን ችግኞች ገደማ መተከላቸውን ለአብነት አንስተዋል። እንዲሁም በቡና እንክብካቤ ሥራ የተሻለ አፈፃፀም በመታየቱ አበረታች ውጤት መመዝገቡን አንስተው፤ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህም 9 ሺህ 458 ኩንታል የቡና ምርጥ ዘር፣ 3 ነጥብ 15 ቢሊየን የቡና ችግኝ፣ 25 ሺህ ዲቃላ የቡና ችግኝ ባለፉት ሥድስት ወራት ብቻ ለተጠቃሚዎች መቅረቡን አብራርተዋል። በቡና ማሳ ላይ የበሽታና ተባይ አሰሳ፣ የቡና ግንድ አድርቅ እና የቡና ፍሬ በሽታ መከላከል እንዲሁም የቡና አረም ቁጥጥር ተግባራት መከናወናቸውን ጨምረው ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency
የባህር ዳር ከተማን የቱሪዝም መዳረሻነት የበለጠ ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ናቸው
Jan 10, 2026 97
ባህርዳር ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ የባህር ዳር ከተማን የቱሪዝም መዳረሻነት የበለጠ ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ተስፋ ሰጪ መሆናቸውን በብልጽግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር) ገለጹ። የብልጽግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ አመራሮች በባህር ዳር ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን ዛሬ ማምሻውን ጎብኝተዋል። የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊው ሰማ ጥሩነህ (ዶር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ የባህር ዳር ከተማን ይበልጥ በማዘመን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ የተሰሩ ስራዎች አበረታች ናቸው። የከተማ አስተዳደሩ ነዋሪውን በማስተባበር በኮሪደር ልማት፣ በስታዲየም ግንባታ፣ የአስፋልት መንገድ ግንባታ፣ በአረንጓዴ ስፍራዎችና ሌሎች የልማት ስራዎች ያከናወነው የልማት ስራ የሚደነቅ ነው ብለዋል። ይህም ከተማዋን ከሀገር አቀፍና ከሌሎች የአለም ከተሞች ጋር በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የቱሪስት መስህቧ ተወዳዳሪ እንድትሆን ማድረጉን በምልከታቸው ማረጋገጣቸውን ተናግረዋል። የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው እንደገለጹት፤ ከተማዋን የበለጠ የቱሪዝምና ኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ በርካታ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ ነው። በከተማዋ እየተገነባ ያለው የኮሪደር ልማት ለኑሮ፣ ለመዝናኛና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ አድርጓታል ብለዋል። ስማርት ባህርዳርን በመተግበር፣ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎትን እውን በማድረግ ህብረተሰቡ የሚያነሳቸውን የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። አመራሮቹ የኮሪደር ልማት፣ አዲሱን የአባይ ድልድይ እንዲሁም በጣናነሽ ቁጥር 2 ጀልባ በጣና ሃይቅ ላይ ሽርሽር በማድረግ ሌሎች የመሰረተ ልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል።
የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ የአፍሪካ አቪዬሽን ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት የተወሰደ ትልቅ እርምጃ ነው
Jan 10, 2026 179
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ የአፍሪካን አቪዬሽን እድገት አስሮ የያዘውን የመሰረተ ልማት ችግር በዘላቂነት ለመፍታት የተወሰደ ትልቅ እርምጃ ነው ሲሉ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ገለፁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታን ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታው በሁለት ምዕራፎች ተከፍሎ የሚከናወን ነው። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ለኢትዮጵያ የሎጂስቲክስ ስርዓት የዘመናት ስብራት ምላሽ የሚሰጥ ነው በመጀመሪያው ምዕራፍ የሚገነባው አውሮፕላን ማረፊያ በዓመት 60 ሚሊዮን መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል ብለዋል። በዚህ ምዕራፍ አንድ እጅግ ትልቅና ዘመናዊ እንዲሁም አንድ መለስተኛ የመንገደኞች ማስተናገጃ ተርሚናሎች እንደሚገነቡ ጠቅሰዋል። ሁለት በተጓዳኝ የሚሰሩ የአውሮፕላን መንደርደሪያዎች እንዲሁም 180 አውሮፕላኖችን በአንድ ጊዜ ማቆም የሚያስችል ቦታ ይገነባልም ብለዋል። በተጨማሪ 350 ማረፊያ ክፍሎች ያሉት ዘመናዊ ሆቴል በተርሚናሉ ውስጥ እንደሚገነባም ነው ዋና ሥራ አስፈፃሚው የተናገሩት። በዓመት አንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ቶን ጭነት የሚያስተናግድ የካርጎ ተርሚናል እና የአውሮፕላን ጥገና ማዕከልም በዚሁ ምዕራፍ እንደሚገነባ አስታውቀዋል። አዲሱ አውሮፕላን ማረፊያ ከነባሩ የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጋር በፈጣን ባቡር እና በፈጣን የመኪና መንገድ እንደሚገናኝ አስረድተዋል። ይህ ግዙፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ የአፍሪካን አቪዬሽን እድገት አስሮ የያዘውን የመሰረተ ልማት ችግር በዘላቂነት ለመፍታት የተወሰደ ትልቅ እርምጃ ነው ሲሉ ገልፀዋል። ፕሮጀክቱ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ አህጉርም ትልቅ አርአያ እንደሚሆን ተናግረዋል።። በተለይም የአፍሪካ ነፃ አህጉራዊ ንግድ ቀጣናን ተግባራዊነት ለማቀላጠፍና የአህጉሪቱን የንግድና የኢኮኖሚ ትስስር ለማጠናከር ቁልፍ ሚና ይጫወታል ብለዋል። አውሮፕላን ማረፊያው ከፍተኛ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር የገለጹት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ ከአውሮፕላን ማረፊያው ጋር ተያይዞ የሚመሰረተው የኤርፖርት ከተማም በንግድ፣ በኢንዱስትሪና በቱሪዝም ዘርፎች ለአካባቢው ዕድገት ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አብራርተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የመሠረተ ልማትና ፕላኒንግ ክፍል ኃላፊ አቶ አብረሃም ተስፋዬ በበኩላቸው፤ አካባቢው አሁን ለሚሰራውም ሆነ ለወደፊት ተያያዥ የማስፋፊያ ስራዎች አመቺ እንደሆነ ገልፀው፤ ቦታው ለታለመለት ግዙፍ ፕሮጀክት ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ እንዳለው አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅት የመሬት ጠረጋ (Earthwork) ስራዎችን የሚያከናውነው ኮንትራክተር ወደ ስራ ገብቷል ብለዋል። የመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ እ.ኤ.አ በ2030 እንደሚጠናቀቅ ጠቁመው፤ ለዋናው ግንባታ የሚሆኑ ተቋራጮችን የመምረጥ ሂደትም መጀመሩን ተናግረዋል።
የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ለኢትዮጵያ የሎጂስቲክስ ስርዓት የዘመናት ስብራት ምላሽ የሚሰጥ ነው
Jan 10, 2026 152
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ለኢትዮጵያ የሎጂስቲክስ ስርዓት የዘመናት ስብራት ምላሽ የሚሰጥ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታን ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። የአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታ በሁለት ምዕራፍ የሚከናወን ሲሆን፤ ግንባታው ሲጠናቀቅ በዓመት 110 ሚሊየን መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል። የመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ 60 ሚሊየን መንገደኞች የማስተናገድ አቅም በመያዝ እንደ አውሮውፓውያን አቆጣጠር በ2030 እንደሚጠናቀቅም ነው የተገለጸው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፉት 80 ዓመታት የጥንታዊ ሀገር ምልክትና ኩራት ሆኖ ስኬታማ ስራ ማከናወኑን ተናግረዋል። አየር መንገዱ በእነዚህ ዓመታት ያለፈባቸው መንገዶች አልጋ በአልጋ እንዳልነበሩ አስታውሰው፤ በኢትዮጵያ ያጋጠሙ የመንግስት ስርዓት መለዋወጥም ሆኑ ሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ሳይበግሩት በከፍተኛ ብቃት የአፍሪካ ኩራት መሆን መቻሉንም አብራርተዋል። ከአየር መንገዱ የስኬታማነት ጉዞ ጀርባ ያለው ታላቅ ምስጢር ደግሞ ጠንካራ የኮርፖሬት ባህል መገንባት መቻሉ መሆኑንም አንስተዋል። በዚህም አየር መንገዱ ጥቅሙን ባስጠበቀ መልኩ ያለምንም ጣልቃ ገብነት ነጻ ሆኖ በዓለም አቀፍ የቢዝነስ ህግ እየተመራ መቀጠሉን ነው የተናገሩት። ለደህንነት ቅድሚያ የሚሰጥ፣ በፈጠራና ትጋት የሚሰሩ አመራሮች፣ በተደመረ አቅም የኢትዮጵያን ሰንደቅ ዓላማ በትጋትና ሃላፊነት የሚሸከሙ ሰራተኞች ያሉት መሆኑን አውስተው፤ ተቋሙ ዘወትር ለመማር ዝግጁ መሆኑ ደግሞ አየር መንገዱን ልዩ እንደሚያደርገውም አብራርተዋል። ዛሬ ግንባታው የተጀመረው የአውሮፕላን ማረፊያው በዓመት 110 ሚሊዮን መንገደኞችን በማስተናገድ በዓለም ላይ ካሉ ጥቂት ግዙፍ አውሮፕላን ማረፊያዎች አንዱ እንደሚሆን ተናግረዋል። አዲስ የሚገነባውን አውሮፕላን ማረፊያ ከቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጋር የሚያገናኝና በአንድ ጊዜ 12 ተሽከርካሪ ማስተናገድ የሚችል የፍጥነት መንገድ እንዲሁም ፈጣን የባቡር መንገድ እንደሚገነባም ገልጸዋል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ በሰማይ ለሚበሩ መርከቦቻችን እንደ ትልቅ ወደብ ሆኖ ያገለግላል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህም ለኢትዮጵያ የሎጂስቲክስ ስርዓት የዘመናት ስብራት ምላሽ የሚሰጥ ስለመሆኑ አብራርተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በርካታ ፈተናዎችን ተቋቁሞ ስኬታማ እንደሆነ ሁሉ የሚገጥሙን ፈተናዎች ይበልጥ እንድንተጋ እና ለስኬታችን እንድንጸና ያደርጉናል ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከ140 በላይ ዓለም አቀፍ መዳረሻዎች ያሉት ግዙፍ ኩባንያ ሲሆን፤ በተያዘው እኤአ 2026 ተጨማሪ አዳዲስ ዓለም አቀፍ መዳረሻዎችን ወደ ስራ እንደሚያስገባም ይጠበቃል።
አየር መንገዳችን የአፍሪካ አስተሣሣሪነቱን የሚያጸና አዲስ ምዕራፍ ጀምሯል - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Jan 10, 2026 139
አዲስ አበባ፤ጥር 2/2018 (ኢዜአ)፦ አየር መንገዳችን ለ80 ዓመታት የዘለቀውን የአፍሪካ አስተሣሣሪነቱን የሚያጸና አዲስ ምዕራፍ ጀምሯል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማሕበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ ጠቅላይ ሚኒስትራችን በጉባ ካበሠሯቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች አንዱ የሆነውንና በአፍሪካ ግዙፉን የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ዛሬ በቢሾፍቱ አስጀምረናል ብለዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከስምንት አስርት ዓመታት በፊት በጥቂት አውሮፕላኖች ጉዞውን ጀመረ፤ ዓላማው ኢትዮጵያን ከዓለም ጋር ማገናኘት ብቻ አልነበረም፤ የአፍሪካን ክብር በሰማይ ላይ ከፍ አድርጎ ማሳየት ጭምር እንጂ ሲሉም አብራርተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የቢሾፍቱ አለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታን በይፋ አስጀመሩ የቢሾፍቱ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በአፍሪካ ታሪክ ትልቁ የአየር ትራንስፖርት መሠረተ ልማት ፕሮጀክት ይሆናል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በዓመት እስከ 110 ሚሊየን መንገደኞችን የማስተናገድ ዐቅም የሚፈጥረው አዲሱ አውሮፕላን ማረፊያ የኩራት ታሪካችንን ወደ አዲስ ምዕራፍ የሚያሸጋግር የኢትዮጵያ ግልጽ ራዕይና የብልጽግና ጉዞ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ የመንግሥታችንን በትልቁ አስቦ በትልቁ የማሳካት ዕይታን የሚገልጥ፣ የአፍሪካን የልዕልና ጉዞ በማረጋገጥ በዓለም አቪዬሽን መሪ ሚና እንዲኖራት የሚያስችል ነው ብለዋል። የአየር መንገዳችንን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ይበልጥ ከፍ የሚያደርገው ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ፋይዳው የላቀ ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ አየር መንገዱ ወደ አፍሪካ መግቢያ እና መውጫ ዋናው በር ሆኖ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያን የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት የማድረግ የፈጠራና ፍጥነት ጉዟችን በሁሉም ዘርፍ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በወላይታ ዞን የሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎች ለስራ ዕድል ፈጠራና ለቴክኖሎጂ ሽግግር እገዛ እያደረጉ ነው
Jan 10, 2026 132
ወላይታ ሶዶ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ በወላይታ ዞን የሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎች ለስራ ዕድል ፈጠራና ለቴክኖሎጂ ሽግግር ትልቅ እገዛ እያደረጉ መሆኑን የዞኑ ንግድና ኢንዳስትሪ ልማት መምሪያ ገለጸ። የወላይታ ዞን ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት መምሪያ ኃላፊ ወይንሸት ሞላን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት ለማሳደግ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ እና ክትትል እየተደረገ ነው። በተለይም በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በተለያዩ ምክንያት ምርታማነታቸው የቀነሰና ያቆሙ ኢንዱስትሪዎችን ወደ ስራ ለማስገባት በየደረጃው ከሚገኙ ተቋማትና ባለ ድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት መሰራቱን አንስተዋል። በዚህም ከ2015 ዓ.ም ጀምሮ ከ1 ሺህ 24 በላይ አነስተኛ እና መካከለኛ ደረጃ ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ ገብተዋል ብለዋል። ተግባሩን በማጠናከርም ባለፉት 6 ወራት ብቻ ከ20 በላይ አነስተኛ እና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ በመግባት ለስራ እድል ፈጠራና ተኪ ምርትን በማምረት ላይ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ዘርፉ ከፈጠረው የስራ ዕድል በተጨማሪ የዕውቀትና ክህሎት ሽግግር እንዲኖር ማስቻሉን ተናግረዋል። በወላይታ ዞን ወደ ስራ በገቡ አምራች ኢንዱስትሪዎች የስራ እድል ተጠቃሚ የሆኑ ወጣቶች እንዳሉት ኢንዱስትሪዎቹ የስራ እድልን ከመፍጠራቸው ባለፈ ክህሎታቸውን እንዲያዳብሩ አግዘዋቸዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል የቦዲቲ ከተማ ነዋሪ ወጣት ፀጋዘአብ ዘሪሁን እንደገለጸው፤ በከተማው የታሸገ ውኃ በሚያመርት ፋብሪካ የስራ ዕድልን በማግኘቱ ራሱንና ቤተሰቦቹን እየደጎመ ነው። በኢንዳስትሪው ያገኘው እድል ከአዲስ ቴክኖሎጂ ጋር እንዲተዋወቅ እድል እንደፈጠረለት አክሏል። ከስራ እጥነት ወደ ስራና የሙያ ባለቤት የተቀየረው ሌላው የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪ ወጣት አሳምነው ዘሜ በበኩሉ፤ በተመረቀበት የኤሌክትሪካል ኢንጂነሪንግ ዘርፍ በዱቄት ፋብሪካ ተቀጥሮ እየሰራ መሆኑን አንስቷል። በፋብሪካው ካገኘው የስራ እድል ባለፈ ከዘመናዊ ቴክኖሎጂ ጋር እንዲተዋወቅና ሙያውን እንዲያሳድግ እንዳገዘው ተናግሯል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የቢሾፍቱ አለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታን በይፋ አስጀመሩ
Jan 10, 2026 143
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የቢሾፍቱ አለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታን ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ባወጣው መረጃ ኢትዮጵያ እምቅ አቅሟንና ታላቅ ርዕይዋን የሚመጥን ሌላ ተጨማሪ ሜጋ ፕሮጀክት ጀምራለች ሲል ገልጿል። የቢሾፍቱ አለምአቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በአፍሪካ ታሪክ ትልቁ የአየር ትራንስፖርት መሠረተ ልማት እንደሚሆንም አመልክቷል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ከከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ጋር በመሆን የአውሮፕላን ማረፊያውን ግንባታ ይፋዊ በሆነ መርሃ ግብር ዛሬ በስፍራው ማስጀመራቸውንም አስታውቋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በንግግራቸው እለቱ ኢትዮጵያ ወደ ዘመናዊነት እና ብልጽግና የምታደርገው ጉዞ አንድ እጥፋት ነው በማለት እንደገለጹት ጽህፈት ቤቱ አመልክቷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድም የሀገር የኩራት ምንጭ መሆኑን አውስተው ይኽ የሆነው ግን ያለተግዳሮት በመጓዙ ሳይሆን በጽናት በተሞላው እንቅፋቶችን የመሻገር አቅሙ እና በአፍሪካ የፋና ወጊነት ሚናው የተነሳ መሆኑን ገልጸዋል። የአየር መንገዱ ትልቁ ጥንካሬ የሚመነጨው ከጠንካራው ተቋማዊ ባሕሉ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ማንሳታቸውንም አመልክቷል። ለጥንቃቄ እና ደኅንነት ቅድሚያ መሥጠት፣ በፈጠራ እና ጠንካራ ሥራ የሚመራ አመራር፣ ከ26,000 በላይ ቁጥር ያለው በአየር መንገዱ ሰንደቅ ተሸካሚነት እና የሚወክለውን የሚያምኑ እና የሚያከብሩ ሠራተኞች እንዲሁም ያላሰለሰ የመማር እና የአቅም ግንባታ ጥረት የተቋሙ የትልቅ የጥንካሬ እና ጠንካራ ተቋማዊ ባህል እንዲገነባ ማስቻሉን መናገራቸውን አስታውቋል። ከአዲስ አበባ ደቡብ ምዕራብ በ40 ኪሎሜትር ርቀት በ1910 ሜትር ከፍታ ላይ የምትገኘው ቢሾፍቱ ለአውሮፕላኖች የተመቸ ከባቢ ብሎም ኢትዮጵያን መዳረሻ ለሚያደርጉም ሆነ ለትራንዚት መንገደኞች ምቹ አቀባበል የተመቸች እንደሚያደርጋት ነው ጽህፈት ቤቱ ያስታወቀው። ፕሮጀክቱ ብዛት ያላቸው የተሽከርካሪ መስመሮችን የያዘ አዲስ አበባን ከአዲሱ አውሮፕላን ማረፊያ የሚያገናኝ ዘመናዊ መንገድ ግንባታን ያካተተ ሲሆን በሰዓት ከ120-200 ኪሎ ሜትሮች ፍጥነት ያለው የከፍተኛ ፍጥነት የባቡር ሀዲድ እና ሥርዓት ግንባታንም አካትቷል። በመጀመሪያው ምዕራፍ የቢሾፍቱ አለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በአመት 60 ሚሊዮን መንገደኞችን ለማስተናገድ የሚችል ሲሆን በታቀደው መሠረት ሙሉ ግንባታው በሚጠናቀቅበት ወቅትም በአመት እስከ 110 ሚሊዮን መንገደኞችን ያስተናግዳል። ይኽም ኢትዮጵያን ከአለም ግንባር ቀደም የአየር ትራንስፖርት ማዕከላት አንዷ እንደሚያደርጋት ጽህፈት ቤቱ አስታውቋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለቀጣናዊ ትብብር እና የኃይል ትስስር ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል
Jan 10, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በራስ አቅም ግዙፍ ፕሮጀክቶችን የመገንባት ተምሳሌት ከመሆን ባለፈ ለቀጣናዊ ትብብር እና የኃይል ትስስር ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በኢትዮጵያውያን የተባበረ ክንድና በይቻላል መንፈስ እውን መሆኑ ይታወቃል። ይህም ኢትዮጵያ ከራሷ አልፋ ጎረቤት ሀገሮችን ጭምር በኃይል አቅርቦት ተደራሽ በማድረግ ለአፍሪካ አንድነትና ትስስር ያላትን ሚና በማጎልበት በኩል የላቀ አበርክቶ አለው። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውኃ፣ መስኖና ቆላማ አካባቢ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢና የፓን አፍሪካ ፓርላማ አባል አወቀ አምዛዬ(ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያውያን በዓድዋ የሰሩት ታላቅ የአንድነት ገድል ለጥቁር ሕዝቦች ሁሉ አርአያ የሆነና ከቀኝ ግዛት እንዲውጡ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረከተ መሆኑን አስታውሰዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እንደ ዓድዋ ሁሉ የኢትዮጵያውያን አንድነትና አብሮነት የተገለጠበት ከመሆኑ ባለፈ ሜጋ ፕሮጀክቶችን በራስ አቅም እውን ማድረግ እንደሚቻል ያሳየና ለአፍሪካ ሀገራትም ትልቅ መነቃቃት የፈጠረ ነው ብለዋል። ግድቡ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ሌሎች የአፍሪካ ሀገራትን ጭምር በኃይል አቅርቦት በማስተሳሰር ኢትዮጵያን ለአፍሪካ አንድነትና አብሮነት ወሳኝ የትብብር ማዕከል እንዳደረጋት ተናግረዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል አምባሳደር የሺ መብራት መርሻ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሕዳሴ ግድብ የኢትዮጵያውያን የትብብራችንና የአንድነታችን ውጤት ነው ብለዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የሀገርን ሃብት ለልማት ማዋል የተቻለበት መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። በአንድነትና በአብሮነት ትልቅ ተዓምር መስራት እንደሚቻል ሕዳሴ ግድብ ትልቅ ትምህርት የሰጠ በመሆኑ ትብብራችንን ማጠናከር ይኖርብናል ሲሉም አስገንዝበዋል።