ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማትን ይበልጥ ተወዳዳሪ አድርጓል
May 26, 2026 50
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማትን ይበልጥ ተወዳዳሪ ለማድረግና የህብረተሰብ ተሳትፎን ለማሳደግ ያስቻለ መሆኑን የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ ገለፁ። የካፒታል ገበያ ለሀገሪቱ ኩባንያዎች የረጅም ጊዜ ካፒታል ምንጭ የሚያስገኝና የፋይናንስ አማራጭን በማስፋት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መረጋጋት የሚደግፍ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮ-ቴሌኮም በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ መመዝገቡን ይፋ ያደረገ ሲሆን ይህም ባለአክሲዮኖች በሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ አክስዮናቸውን እንዲያስተዳድሩ፣ እንዲገዙና እንዲሸጡ የሚያስችል ነው።   በምዝገባ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ፣ የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጥላሁን እስማኤል (ዶ/ር)፣ የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እንዲሁም የብሔራዊ ባንክና የሌሎች ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ እንደገለጹት፤ ሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ የኢኮኖሚ መዋቅሩን ማዘመን፣ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማሳደግ፣ የመንግሥት ልማት ድርጅቶችን ተወዳዳሪነትና የሕብረተሰቡን ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል ነው። የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማት ለበርካታ ዓመታት ሙሉ በሙሉ በእጅ ስር እንደነበሩ አስታውሰዋል። የኢኮኖሚ ማሻሻያው ይህን አካሄድ በመቀየር ተቋማቱ ይበልጥ ተወዳዳሪ እንዲሆኑና የህዝብ ተሳትፎ እንዲያድግ በር ከፍቷል ብለዋል። በዚህም ኢትዮ-ቴሌኮም የባለቤትነት ይዞታውን ክፍት በማድረግ የመጀመሪያው የመንግስት የልማት ድርጅት በመሆን በሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ በይፋ መመዝገቡን ተናግረዋል። ምዝገባው ለወራት ሲካሄድ የቆየ የዝግጅት ውጤት መሆኑን ጠቅሰው ባለስልጣኑ ሂደቱ ግልፅነትና ዓለምአቀፍ አሰራር የተከተለ እንዲሁም የኢንቨስተሮችን መብት የሚያስጠብቅ እንዲሆን ሲሰራ መቆየቱን አስታውቀዋል። የካፒታል ገበያ መመስረትና ማደግ በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎችን የሀገሪቱ ግዙፍ ድርጅቶች ባለድርሻ የሚያደርግ ነው ብለዋል። የካፒታል ገበያ ለሀገሪቱ ኩባንያዎች የረጅም ጊዜ ካፒታል ምንጭ የሚያስገኝና የፋይናንስ አማራጭን በማስፋት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መረጋጋት እንደሚደግፍም ተናግረዋል። በሂደት ላይ ያሉ ተቋማትም የድርጅት አስተዳደራቸውን በማሻሻል ወደዚህ መድረክ እንዲመጡና የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ምህዳር ይበልጥ እንዲሰፋና አማራጭ የካፒታል ምንጭ ለማግኘት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል።   የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጥላሁን እስማኤል (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮ- ቴሌኮም ወደ ዘመናዊ የሰነደ ሙዓለ ነዋይ ግብይት መግባት ለሥራቸው ታላቅ አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። አያይዘውም ባለአክሲዮኖች ወደ ዘመናዊ የኤሌክትሮኒክስ መገበያያ ሥርዓት መግባታቸውንና የንግድ አካውንት በመክፈት በአገናኝ አማካኝነት መገበያየት እንደሚችሉ ጠቁመዋል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ፤ ኢትዮ-ቴሌኮም የ10 በመቶ ድርሻውን ለዜጎች መሸጡን ተከትሎ የባለአክሲዮኖችን መረጃ የመሰነድና የማደራጀት ሥራ በማከናወን በኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን አጸድቋል ብለዋል።   በዚህም አክሲዮን ከገዙ 47ሺህ 377 ባለአክሲዮኖች 10 ነጥብ 7 ሚሊዮን አክሲዮኖችን በመሸጥ 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። ከእነዚህ መካከል የ45 ሺህ ያህሉ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ 10 ነጥብ 1 ሚሊዮን አክሲዮን በ3 ቢሊዮን ብር ለባለ አክሲዮንነት ብቁ ሆነው በመገበያያ ማዕቀፉ መካተታቸውን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት የ96 በመቶ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ የዲጂታል ባለቤትነት ማረጋገጫ ማግኘት መቻላቸውን ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም መድረክ ጠንካራ የተወዳዳሪነት አቅም የገነባ ተቋም ነው - አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ
May 26, 2026 67
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም መድረክ ጠንካራ የተወዳዳሪነት አቅም የገነባ ተቋም መሆኑን በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከቀናት በፊት የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን በተለያዩ ሆነቶች በደማቅ መርሃ ግብር አክብሯል። በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት ተቋማዊ ዕድገትን ማስቀጠል እያስቻሉት ነው። አየር መንገዱ በገነባው የረጅም ዘመናት ዓለምአቀፍ ስምና ዝናም ከአሜሪካ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ኩባንያዎች ጋር ጠንካራ የትብብር አጋርነት እንዳለው ገልጸዋል። ለአብነትም በዓለም አቀፍ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሆኑት ከቦይንግና ጂኢ-ኤሮስፔስ የአሜሪካ ኩባንያዎች ጋር ጥብቅ አጋርነት ያለው ተቋም መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ዘርፍ አፍሪካን ከቀሪው ዓለም የሚያስተሳስር አስደናቂና ግዙፍ መሰረተ ልማት በማስፋፋት ላይ የምትገኝ ሀገር መሆኗንም አንስተዋል። በዚህም የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአዳዲስ የመንገደኛ አውሮፕላን፣ የበረራ መዳረሻ በማስፋትና በሀገር ውስጥ የአየር ማረፊያ መሠረተ ልማት ግንባታ አስደናቂ ሥራ እየሰራ መሆኑን አብራርተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የገነባው አቅም ቀጣናዊ አየር መንገድ ብቻ ሳይሆን በዓለም መድረክ ላይ ተወዳዳሪ እንዲሆን ማስቻሉን ገልጸዋል። የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅትን ጨምሮ በአስቸጋሪ ወቅቶች በአሜሪካና በኢትዮጵያ አየር መንገድ መካከል የተገነባው ጠንካራ ግንኙነት ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። በኮቪድ ወረርሽኝ ወቅትም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከአሜሪካ ጋር የነበረው ጠንካራ ትብብርና አጋርነት የክትባትና መድኃኒት ቁልፍ ቁሳቁሶችን በማጓጓዝ ከፍተኛ ሚና እንዲወጣ ማስቻሉን አስታውሰዋል። የአየር መንገዱ የወደፊት ዕቅድና የአቅም ግንባታ የትኩረት መስክ ለቀጣይ ስኬቱ ቁልፍ እንደሚሆኑም አምባሳደሩ ጨምረው ገልጸዋል። በዚህም በኢትዮጵያ አየር መንገድ የዕድገት ጉዞ ላይ አሜሪካና የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ኩባንያዎቿ አጋርነታቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በኢትዮጵያና አሜሪካ መካከል ያለው ታሪካዊ ግንኙነት በተለያዩ የልማትና የትብብር መስኮች እየተጠናከረና እያደገ መምጣቱን አስረድተዋል።
በኦሮሚያ ክልል ከተሞች የማህበረሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት ተደርጓል
May 26, 2026 49
መቱ፣ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ከተሞች የነዋሪውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ላይ በትኩረት በመሰራቱ የተሻለ ውጤት መገኘቱ ተገለጸ። በመቱ ከተማ ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 48 የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል።   በክልሉ ከተሞች የሚከናወኑ የሕንጻዎችና የመሠረተ ልማት ግንባታዎች ምቹ የመኖሪያና ማሕበራዊ አካባቢዎችን ለመፍጠር፣ የመሠረተ ልማት አውታሮችን ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም ቀልጣፋና ዘመናዊ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓትን ለማስፈን ያለሙ መሆናቸውም ተገልጿል። በምረቃ መርሐግብሩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ግርማ ረጋሳ እንደገለጹት፤ በክልሉ ከተሞች በቂ የመሰረተ ልማት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። ፍትሐዊና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓት ከማስፈንና የማሕበረሰቡን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አንጻር በርካታ ተግባራት መከናወናቸውንም ጠቁመዋል። ኃላፊው አክለውም፣ በክልሉ በየጊዜው እየተገነቡ ለአገልግሎት ክፍት የሚሆኑ የልማት ፕሮጀክቶች ዜጎች የተሻለ ሕይወት እንዲመሩ የሚያስችሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል።   የመቱ ከተማ ከንቲባ አቶ ተሻለ ኤጄርሶ በበኩላቸው፣ ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት 48 ፕሮጀክቶች መካከል የትምህርት ቤቶች ግንባታና የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶችን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የመንገድ ዳር የኮሪደር ልማት ስራዎች፣ የንግድ መስሪያ ቦታ ሼዶች፣ የከተማ ግብርና ማዕከላት፣ የኤሌክትሪክ መስመሮች ዝርጋታ እና የከተማ አስተዳደር ሕንጻም መመረቁን ተናግረዋል። ከንቲባው ፕሮጀክቶቹ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ከማዘመንና ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ፣ የሕብረተሰቡን ማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግና ከተማዋን ውብና ምቹ የመኖሪያ አካባቢ ለማድረግ የሚረዱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የመቱ ከተማ ነዋሪዎች መካከል አቶ አብዱራህማን ኢድሪስ እና አቶ ተስፋዬ ኮንቺ ግንባታው ተጠናቆ ወደ አገልግሎት የገባው የከተማ አስተዳደሩ ሕንጻ የከተማዋን ገጽታ የሚያሳድግ ከመሆኑም በላይ፣ ቀልጣፋ፣ ዘመናዊና ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። ወይዘሮ ኑሪያ ሁሴን እና አቶ መሐመድጣሂር አባገሮ በበኩላቸው የተገነቡት ሼዶች የሥራ ዕድል የሚፈጥሩና ሠርተው የሚለወጡበትን ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው ብለዋል። የመንገድ ዳር የኮሪደር ልማቱ የትራፊክ ፍሰቱ የተሳለጠ እንዲሆንና አደጋ እንዲቀንስ ከማድረጉም በላይ፣ የከተማዋን ውበት በመጨመር ለመኖሪያነት ምቹ አድርጓታል ብለዋል።  
የከተማውን አገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን ለንግድና ኢንቨስትመንት የበለጠ ምቹ ለማድረግ ትከረት ተሰጥቷል
May 26, 2026 138
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በወላይታ ሶዶ ከተማ የመንግስት አገልግሎትን በማዘመን ከተማውን ለንግድና ኢንቨስትመንት የበለጠ ምቹ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ ። የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር ከ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ለሚያስገነባው የባለ 12 ወለል የቢሮ ሕንፃ ግንባታ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ዛሬ ተካሂዷል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ በወቅቱ እንደገለጹት የወላይታ ሶዶ ከተማ ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ እየሆነች መምጣቷን ተከትሎ አገልግሎት አሰጣጡን ማዘመን አስፈልጓል። ግንባታው የተጀመረው የከተማ አስተዳደሩ የቢሮ ህንጻ ምቹ የሆነ የስራ አካባቢ በመፍጠር የመንግስት አገልግሎት አሰጣጡን ለማዘመን የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል ። የአገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን ከተማዋን ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ ለማድረግ በሚደረገው ሂደት በቅንጅትና በትብብር መስራት አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል።   የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማርያም በከተማ አስተዳደሩ ምቹ የስራ አካባቢ ለመፍጠር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የሚገነባው ዘመናዊ የቢሮ ህንፃ የዚሁ አካል መሆኑን ጠቁመው ህንጻው ከተማዋን ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭና ተወዳዳሪ ለማድረግ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል፤ የቢሮ ህንጻው በ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር የሚገነባ መሆኑን ጠቁመው ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ አስታውቀዋል ።      
ከተማ አስተዳደሩ የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን በልዩ ትኩረት እያከናወነ ነው
May 26, 2026 110
አዳማ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- የአዳማ ከተማ አስተዳደር የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን በልዩ ትኩረት እያከናወነ መሆኑን የከተማው ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ ገለጹ። በአዳማ ከተማ በ17 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ።   የልማት ፕሮጀክቶቹን በዛሬው ዕለት በይፋ የመረቁት የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ እና የኦሮሚያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ አባቢያ ናቸው። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ አቶ ኃይሉ ጀልዴ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ የቤተሰብ ብልጽግናን፣ የሥራ ዕድል ፈጠራን፣ የገበያ ማረጋጋትንና ማኅበራዊ አገልግሎትን ማዕከል ያደረጉ በርካታ የልማት ሥራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል። በመጀመሪያው የምረቃ ምዕራፍ ዛሬ ከተመረቁት መካከል የመንግስትንና የሕዝብን አቅም በማቀናጀት በ5 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በጀት የተገነቡ 14 የልማት ፕሮጀክቶች ይገኙበታል ብለዋል። እነዚህ ፕሮጀክቶች በትምህርት፣ በጤና፣ በመንገድ መሠረተ ልማት እና በሕዝብ መድኃኒት ቤቶች ላይ ያተኮሩ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ከእነዚህም በተጨማሪ የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ 8 ሺህ ሼዶች በ11 ቢሊዮን ብር ተገንብተው በማኅበር ለተደራጁ ቤተሰቦችና ወጣቶች እየተላለፉ መሆኑን አመልክተዋል። በከተማዋ ኢንዱስትሪ መንደር የተገነቡት እነዚህ ሼዶች ለእንስሳት ማድለብ፣ ለወተት ላም እርባታ፣ ለፍየል ማሞከት፣ ለአሳማና ዶሮ እርባታ እንዲሁም ለሌሎችም ልማቶች አመቺ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በሼዶቹ አማካኝነት ከ80 ሺህ በላይ በኢንተርፕራይዝ የተደራጁ ወጣቶችና አንቀሳቃሾች ተጠቃሚ መሆናቸውን ከንቲባው አስታውቀዋል። አስተዳደሩ ለሥራ ዕድል ፈጠራ የመሥሪያ ቦታ ከማመቻቸት ባለፈ፣ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር የባንክ ብድር እንዲያገኙ በቅንጅት መሥራቱንም ገልጸዋል። ለልማት ፕሮጀክቶቹ ስኬታማነት የከተማው ሕዝብ ላደረገው ከፍተኛ ተሳትፎ ምስጋና ያቀረቡት ከንቲባ ኃይሉ፤ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ሕዝቡ በልማት ሥራዎች ላይ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል።   በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ አባቢያ በበኩላቸው፤ በመንግስት በጀትና በሕዝብ ተሳትፎ የተገነቡና ሕዝብን ማዕከል ያደረጉ ፕሮጀክቶች፣ የለውጡ መንግስት ለሕዝብ የገባውን ቃል በተግባር የሚያሳይ መሆኑን ማረጋገጫ ናቸው ብለዋል። በአዳማ የተመረቁት ፕሮጀክቶች ለከተማው ማኅበረሰብ ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የሚያጎናጽፉ ከመሆናቸውም በላይ፣ የአስተዳደሩን ፕሮጀክቶች ጀምሮ የማጠናቀቅ ግብ በተግባር የሚያሳዩ ሕያው ምስክሮች መሆናቸውን ገልጸዋል። ቀደም ሲል የመሠረተ ድንጋይ የተቀመጠላቸው በርካታ ፕሮጀክቶች እውን ሳይሆኑ የሕዝብ የቅሬታ ምንጭ ሆነው መቆየታቸውን አስታውሰው፤ የለውጡ መንግስት በወሰደው ቁርጠኝነት በርካታ የተጓተቱና አዳዲስ ፕሮጀክቶች በክልሉ ተገንብተው ሕዝቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻላቸውን አብራርተዋል። በዚህ በጀት ዓመትም ለሕዝቡ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መረጋጋት ወሳኝ የሆኑ በርካታ ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን የጠቀሱት ወይዘሮ ሮዛ፤ የተገነቡት ከ21 ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች በየደረጃው የሚገኙ የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን አውስተዋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የክልሉና የከተማዋ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች፣ ነዋሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።  
በክልሉ አምራች ኢንዱስትሪዎችን በመደገፍ ውጤታማነታቸውን የማረጋገጡ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል
May 26, 2026 101
አርባ ምንጭ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አምራች ኢንዱስትሪዎችን በመደገፍ ውጤታማነታቸውን የማረጋገጡ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ተናገሩ። ርዕሰ መስተዳድሩ ከ75 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባውን የአርባ ምንጭ "ያላ አግሮ ኢንዱስትሪ"ን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በምረቃ መርሃግብሩ ላይ እንዳሉት፤ በክልሉ የልማት ጸጋዎችን ለይቶ እሴት ጨምሮ ለማምረት የኢንዱስትሪ ዘርፉን አቅም ማሳደግ ይገባል። ለዚህም አምራች ኢንዱስትሪዎችን በተለያየ መንገድ በመደገፍ እሴት ጨምረው ለገበያ እንዲያቀርቡና ለአርሶ አደሩም የግብይት አማራጭ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። ዛሬ ወደሥራ የገባው ያላ ወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ክልሉ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ለማበረታታት የሚሰራው ተግባር ውጤታማነት ማሳያ መሆኑንም ተናግረዋል። በክልሉ አምራች ኢንዱስትሪዎችን በመደገፍ ውጤታማነታቸውን የማረጋገጡ ተግባር በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። እንደ አቶ ጥላሁን ገለጻ፤ በክልሉ ኢንዱስትሪዎችን ለመሳብ የተቀናጀ ሥራ ከማከናወኑ ባለፈ የአርሶ አደሩን ምርታማነት የሚያሳድጉ የእንስሳት ዝርያን የማሻሻል፣ የእንስሳት ጤናን የመጠበቅ እንዲሁም የእንስሳት መኖ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። የክልሉ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጥላሁን ብርሃኑ በበኩላቸው፤ በክልሉ ያላ የወተት አግሮ ኢንዱስትሪን ጨምሮ 142 አምራች ኢንተርፕራይዞች አሉ። ኢንዱስትሪ ፓርኮቹ እሴት በመጨመርና ተኪ ምርቶችን በማምረት የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለሚደረገው ጥረት እያገዙ መሆናቸውንም አንስተዋል። ይህን በማጠናከር ለሀገር ዕድገት እና ለዜጎች ተጠቃሚነት የአምራች ኢንዱስትሪ ሚና ለማሳደግ በትኩረት እየተሠራ ነው ሲሉም አክለዋል። የያላ አግሮ ኢንዱስትሪ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ አለማየሁ እስራኤል፤ ኢንዱስትሪው በቀን 24 ሺህ ሊትር ጥራት ያለው ወተት ማቀነባበር እንደሚችል ገልጸዋል። ለ150 ዜጎች ቀጥተኛ የሥራ ዕድል የሚፈጥር ሲሆን፤ በእሴት ሰንሰለት ከ5 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ አስረድተዋል። ኢንዱስትሪው ፓስቸራይዝድ ወተት፣ ተፈጥሯዊ እርጎ፣ ቺዝ፣ ክሬም እና አይብ እንደሚያመርትም ተናግረዋል።
በክልሉ በክረምቱ ወራት ከ3 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሻይ ችግኝ ይለማል
May 26, 2026 107
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው ክረምት ከ3 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሻይ ችግኝ በኩታገጠም እንደሚለማ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የፍራፍሬ ልማት ዳይሬክተር አቶ ቻላቸው አዱኛ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ በክልሉ ከለውጡ ዓመታት ወዲህ ለሻይ ልማት ዘርፍ ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል።   ክልሉ ምቹ የአየር ንብረት፣ በቂ የዝናብ መጠንና ለሻይ ተክል ተስማሚ የአፈር ዓይነት ያለው በመሆኑ ለዘርፉ ከፍተኛ አቅም እንዳለው ጠቁመዋል። ይህንን ተከትሎም ልማቱ በስፋት እየተከናወነ የሚገኘው የዞኖቹን መልክዓ ምድርና የአየር ንብረት መሰረት በማድረግ ሲሆን፤ በተለይም በጅማ፣ ኢሉአባቦር እና ቡኖ በደሌ ዞኖች ውስጥ በስፋት እየለማ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ በዘንድሮው ዓመት ከተዘጋጀው 120 ሚሊዮን የሻይ ችግኝ ውስጥ፤ 42 ሚሊዮኑን በ3 ሺህ 168 ሄክታር መሬት ላይ በኩታገጠም ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ነው ያሉት። ለዚህም እንዲረዳ የመሬት ልየታ ተካሂዶ በክላስተር የተደራጀ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት የጉድጓድ ቁፋሮ እና የሻይ ችግኝ ተከላ ስራ እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል። ከዘርፉ የሚገኘውን ተጠቃሚነት ለማሳደግም የተሻሻሉ ዝርያዎች የሚባዙባቸው የሻይ ችግኝ ጣቢያዎች በመንግስትና በአርሶ አደሮች ደረጃ ለተከላ ተዘጋጅተዋል ብለዋል። በዘንድሮው የልማት ስራ 1 ሺህ 250 አርሶ አደሮች የሚሳተፉ ሲሆን፤ የሻይ ተክል ችግኞችን በኩታገጠም አሰራር ዘዴ ለመትከል ሙሉ ዝግጅት አድርገዋል ሲሉም አረጋግጠዋል። እስካሁን ባለው ሂደት በክልሉ በአጠቃላይ 2 ሺህ 700 ሄክታር መሬት በሻይ ተክል መሸፈኑን ጠቁመው፤ ከ1 ሺህ 200 በላይ አርሶ አደሮችም እየተሳተፉበት ይገኛል ነው ያሉት። አርሶ አደሩ ለሚያመርተው የሻይ ምርት አስተማማኝ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ታቅዶ በስፋት እየተሰራ እንደሚገኝም ተጠቅሷል። በክልሉ ምዕራብ አካባቢዎች ባለው ከፍተኛ የዝናብ መጠን ምክንያት የመሬት አሲዳማነት ይከሰታል። የሻይ ተክል ደግሞ ይህንን የአፈር አሲዳማነት ተቋቁሞ ከፍተኛ ምርት መስጠት የሚችል በመሆኑ፣ የአካባቢውን ስነ-ምህዳር ለመጠበቅና የአርሶ አደሩን ገቢ ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራበት ሲሉም ተናግረዋል። ይህ የሻይ ልማት አሲዳማ መሬትን የመቋቋም አቅም ያለው በመሆኑ፤ በአሁኑ ወቅት መሰል የአፈር ችግር ባለባቸው በሌሎች የክልሉ አካባቢዎችም ልማቱን ለማስፋፋት ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን አቶ ቻላቸው አዱኛ አስታውቀዋል።
ኢትዮ-ቴሌኮም በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለንዋዮች ገበያ ተመዘገበ
May 26, 2026 182
አዲስ አበባ፤ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮ-ቴሌኮም የ10 በመቶ ድርሻ የገዙ ባለአክሲዮኖች ያላቸውን አክሲዮን ማስተዳደር የሚችሉበትና በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለንዋዮች ገበያ መመዝገቡን ገለጸ፡፡ በምዝገባ መርሃ ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ፣ የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለንዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ጥላሁን እስማኤል፣የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እንዲሁም የብሔራዊ ባንክና የሌሎች ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ እንደገለጹት፤ ሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ የኢኮኖሚ መዋቅሩን ማዘመን፣ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማሳደግ፣ የመንግሥት ልማት ድርጅቶችን ተወዳዳሪነትና የሕብረተሰቡን ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል ነው። ኢትዮ-ቴሌኮም የባለቤትነት ይዞታውን በከፊል ለሽያጭ ክፍት በማድረግ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል። ይህ ተግባር የፋይናንስ አካታችነትን የሚያሳድግ መሆኑን የጠቆሙት ዋና ዳይሬክተሯ፤ የካፒታል ገበያ መመስረትና ማደግ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎችን የሀገሪቱ ግዙፍ ድርጅቶች ባለድርሻ የሚያደርግ ነው ብለዋል። አክለውም የካፒታል ገበያ የኢኮኖሚ ዕድገት ሞተር በመሆኑ ሁሉም ማኅበረሰብ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለንዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ጥላሁን እስማኤል በበኩላቸው፤ የኢትዮ- ቴሌኮም ወደ ዘመናዊ የሰነደ ሙዓለንዋይ ግብይት መግባት ለሥራቸው ታላቅ አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። አያይዘውም ባለአክሲዮኖች ወደ ዘመናዊ የኤሌክትሮኒክስ መገበያያ ሥርዓት መግባታቸውንና የንግድ አካውንት በመክፈት በአገናኞች አማካኝነት መገበያየት እንደሚችሉ ጠቁመዋል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እንዳሉት፤ ኢትዮ-ቴሌኮም የ10 በመቶ ድርሻውን ለዜጎች መሸጡን ተከትሎ የባለአክሲዮኖችን መረጃ የመሰነድና የማደራጀት ሥራ በማከናወን በኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን አጸድቋል። በዚህም አክሲዮን ከገዙ 47 ሺህ 377 ባለአክሲዮኖች 10 ነጥብ 7 ሚሊዮን አክሲዮኖችን በመሸጥ 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። ከእነዚህ መካከል የ45 ሺህ ያህሉ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ 10 ነጥብ 1 ሚሊዮን አክሲዮን በ3 ቢሊዮን ብር ለባለአክሲዮንነት ብቁ ሆነው በመገበያያ ማዕቀፉ ውስጥ መካተታቸውን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት የ96 በመቶ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ የዲጂታል ባለቤትነት ማረጋገጫ ማግኘት መቻላቸውን ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ አስታውቀዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ምርጫ
በክልሉ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለምግብነት የሚውሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች በስፋት ተዘጋጅተዋል
May 26, 2026 95
አዳማ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለምግብነት የሚውሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች በስፋት መዘጋጀታቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል ሙዝ፣ አቮካዶ፣ ፓፓያ፣ ብርቱካን፣ ዘይቱን፣ ሎሚ፣ አፕል፣ ማንጎ፣ ግሽጣና ቴምር ይገኙበታል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሙሐመድሳኒ አሚን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደጉ ይገኛሉ። የዚሁ አካል የሆነውን የሙዝ ልማት ይበልጥ ለማሳካትና ምርጥ የሙዝ ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ፣ ባቱን ጨምሮ ከተለያዩ የክልሉ የግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።   ለአብነትም ባለፉት ዓመታት ከ58 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሙዝ ልማት የተሸፈነ ሲሆን፤ ሥራውን አጠናክሮ ለማስቀጠል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ60 ሚሊዮን በላይ የሙዝ ችግኞች በምርምር ማዕከላትና በአርሶ አደሩ ማሳዎች ላይ እንዲባዙ ተደርጎ ለተከላ ተዘጋጅተዋል ብለዋል። የሙዝ ልማቱን ስኬታማ ለማድረግ ከክረምት ወቅት ባለፈ፤ በተለያዩ የክልሉ ዞኖች የበጋ መስኖ ልማት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ልማቱን በማስፋፋት ረገድ ከዚህ ቀደም የሙዝ ምርት በማይታወቅበት በምሥራቅ ሸዋ ዞንና በሌሎች የክልሉ ቆላማ አካባቢዎች ጭምር በስፋት እየለማ መሆኑን ገልጸዋል። የሙዝ ልማቱ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም ባለፈ፤ አማራጭ የገቢ ምንጭን ለማስፋትና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በመደገፍ ረገድ ወሳኝ ሚና እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። ለፓፓያ ልማትም 100 ሚሊዮን የሚጠጉ ችግኞች የተዘጋጁ ሲሆን፤ እነዚህን ችግኞች ከአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጋር የማስተሳሰር ሥራ ተጀምሯል ነው ያሉት። በተጨማሪም በክልሉ የፍራፍሬ ልማትን ይበልጥ ለማስፋፋት የአቮካዶ፣ የብርቱካን፣ የዘይቱን፣ የሎሚ፣ የአፕል፣ የማንጎ፣ የግሽጣና የቴምር ችግኞችን በጥራት የማዘጋጀት ሥራ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ምክትል ኃላፊው አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያረጋግጡ ውጤታማ እርምጃዎችን እየወሰደች ነው
May 25, 2026 753
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያረጋግጡ ውጤታማ እርምጃዎችን እየወሰደች መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ፍትሐዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በዓለም አቀፍ ማዕቀፍ የዲፕሎማሲ መርህ መሳካት የሚችል የህልውና ጉዳይ መሆኑን አስገንዝበዋል። ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያረጋግጡ ውጤታማ እርምጃዎችን እየወሰደች ትገኛለች። የኢትዮጵያ ፍትሕዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄም ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስርን ለመፍጠር ከምታደርገው ጥረት ጋር ተለይቶ የሚታይ እንዳልሆነ አስረድተዋል። በኢትዮጵያዊያን የጋራ መስዋዕትነት በተገነባው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የሚመነጨውን የኤሌክትሪክ ኃይል ለቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም በአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ስትራቴጂ መነሻነት አህጉራዊ ኢኮኖሚያዊ ውህደትን ለማፋጠን ኢትዮጵያ ፀጋዎቿን በመጠቀም በቁርጠኝነት እንደምትሰራ ነው ያመለከቱት። ኢትዮጵያ ከቀይ ባሕር ጋር ያላትን ቁርኝት ተፈጥሮን ከመልክዓ ምድራዊ ታሪካዊነትን ከሕጋዊነት ያሰናሰለ መሆኑን አስረድተው፤ የባሕር በር ባለቤትነቷን እንድታጣ የተደረገበት በሴራና ተንኮል የተሸረበ አካሄድም የሚያስቆጭና ኢትዮጵያን ደካማ ለማድረግ ካለ እሳቤ የመነጨ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ፀጋዋን በመጠቀም ዕድገትን ካረጋገጠች ስጋታችን ትሆናለች የሚለው ስሌትም የታሪካዊ ጠላቶች ኋላቀርና የተሳሳተ ደምዳሜ ነው ብለዋል። በዚህም የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ታሪካዊ መሠረተ ያለው፣ ተፈጥሯዊና መልክዓ ምድራዊ እውነታ ያለው ሕጋዊና ፍትሐዊነትን አሰናስሎ የያዘ የህልውና ጉዳይ ነው ብለዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ የላቲን አሜሪካ ሀገራት ቦሊቪያና ፔሩ፣ ብራዚልና ፓራጓይ፤ በአፍሪካ የማሊ፣ ሴኔጋልና ኮትዲቯር የተጠቀሙባቸውን የጋራ መፍትሔዎች በተሞክሮነት አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ፍትሐዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በዓለም አቀፍ ማዕቀፍ የዲፕሎማሲ መርህ መሳካት የሚችል የህልውና ጉዳይ መሆኑን አስገንዝበዋል። በዚህም የኢትዮጵያ ታሪካዊ፣ ሕጋዊ፣ መልክዓ ምድራዊና ፍትሕዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ማሳካት እንደሚቻል ተናግረዋል። ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ላላት ሀገር የቅንጦት ሳይሆን የኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነትን የሚያስከብር ቁልፍ የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። ለወደብና ሎጂስቲክስ አገልግሎት በየዓመቱ የምታወጣው ከፍተኛ ሃብት ዓለም አቀፍ የንግድ ተወዳዳሪነትና በጠቅላላው የዕድገት ጉዞ ላይ ትልቅ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩን አስገንዝበዋል።
የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹ የመዝናኛ አማራጭ እየፈጠረ ነው
May 25, 2026 459
አሶሳ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹ የመዝናኛ አማራጭ እየፈጠረ መሆኑን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን ተናገሩ። ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን የከተማዋ የኮሪደር ልማት አካል የሆነውን የአሶሳ ሲቲ ፓርክን ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። በዚህ ወቅት ርዕሰ መስተዳድሩ እንደገለጹት፤ በአሶሳ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት በርካታ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላት አብረው እንዲገነቡ አድርጓል።   ልማቱ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹ የመዝናኛ አማራጭ እየፈጠረ መሆኑንም ተናግረዋል። ለዚህም የኮሪደር ልማቱ በሚከናወንባቸው አካባቢዎች በዘመናዊ መልኩ የተገነቡትን የስፖርት ማዘውተሪያ ቦታዎች፣ የሕጻናት መጨዋቻ እና የመዝናኛ ቦታዎች በማሳያነት ጠቅሰው፤ የልማት ሥራዎቹም ለትውልድ የሚተርፉ ናቸው ብለዋል። አሶሳ ሲቲ ፓርክ ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ከመሆኑ ባለፈ ሕፃናት አዕምሯቸው እንዲታደስ የተለያዩ የመዝናኛ አማራጮችን አካቶ መገንባቱንም ተናግረዋል።   የክልሉ መንግስት በሌሎች አካባቢዎችም የኮሪደር ልማቱን ቀጣይነት ባለው መልኩ በማከናወን ለነዋሪዎች ምቹና ጽዱ ከተሞችን ለመፍጠር እየሰራ ይገኛል ብለዋል። የአሶሳ ከተማ ከንቲባ አብዱልከሪም አብዱራሂም በበኩላቸው፤ የአሶሳ ሲቲ ፓርክ የከተማዋን የመዝናኛ ማዕከል እጥረት ችግር የፈታና ለሕፃናትም ልዩ ስጦታ መሆኑ ጠቁመዋል።
ባሕር ዳር ከተማ በልማት ጎዳና ላይ የምታሳየው መነቃቃት የነገ ተስፋችንን በተጨባጭ የሚያሳይ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 25, 2026 492
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 17/2018(ኢዜአ)፦ ባሕር ዳር ከተማ በልማት ጎዳና ላይ የምታሳየው መነቃቃት የነገ ተስፋችንን በተጨባጭ የሚያሳይ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት የተፈጥሮ እውነት ከታሪክ ክብር ጋር በተዋሃደባት፣ በጣና ሐይቅና በዓባይ ወንዝ በታጀበችው የውበት ማማዋ ባሕር ዳር ገብተናል ብለዋል። በመልዕክታቸውም ባሕር ዳር ከተማ በልማት ጎዳና ላይ የምታሳየው መነቃቃት የነገ ተስፋችንን በተጨባጭ የሚያሳይ ነው ሲሉ ገልጸዋል። ባሕር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ስንደርስ፣ ፍቅርና አክብሮት በተሞላበት ሁኔታ ለተደረገልን ደማቅ አቀባበል ለአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር፣ ለክልሉና ለከተማዋ ከፍተኛ አመራሮች፣ በጸሎትና በምርቃታቸው ላልተለዩን የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም ለመላው የባሕር ዳር ሕዝብ ከልብ የመነጨ ምስጋናዬን አቀርባለሁ ብለዋል።  
በኢሉአባቦር ዞን በቴክኖሎጂ የታገዘ ግብርናን በማስፋፋት ምርታማነትን ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ ነው
May 25, 2026 249
መቱ፣ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ):- በኢሉአባቦር ዞን በቴክኖሎጂ የተደገፈ ግብርናን በማስፋፋት ምርታማነትን ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በዞኑ በክረምት እርሻ ከ389 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች የመሸፈን ስራም ተጀምሯል። በክረምት እርሻው በቆሎ፣ ማሽላ፣ ሩዝ፣ አኩሪ አተርና ሌሎች የሰብል ዓይነቶች የሚዘሩ ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው መሬት በኩታ ገጠም የሚታረስ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳሙ ታከለ ተናግረዋል።   ምርታማነትን ለማሳደግም በኩታ ገጠም የማረስ ልማድን በማዳበር እንዲሁም በማዳበሪያና የምርጥ ዘር አቅርቦት ላይ በትኩረት መሰራቱን ኃላፊው ገልጸዋል። ለዚህም ከ161 ሺህ ኩንታል በላይ የኬሚካል ማዳበሪያ እና ከ24 ሺህ ኩንታል በላይ የተለያዩ ምርጥ ዘሮች በክረምት እርሻው በስራ ላይ እንደሚውሉ አስታውቀዋል። ከዚህ ውስጥ 61 ሺህ ሔክታር መሬት በበቆሎ ሰብል የሚሸፈን ሲሆን፤ ለዚሁ ተግባር የሚሆን ከ50 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ መቅረቡንም አክለው ገልጸዋል። በሌላ በኩል በዞኑ ስር በሚገኘው የያዮ ወረዳ በክረምት እርሻ ከ11 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች የመሸፈን ስራ እየተከናወነ መሆኑን የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ በፈቃዱ ኦልጂራ ገልጸዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ ግብርናን በማስፋፋትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። አርሶ አደሮችም በኩታ ገጠም በማረስ ምርታማነታቸውን ለማሳደግ፣ የምግብ ዋስትናቸውንና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ለክረምት እርሻው ከፍተኛ ትኩረት መስጠታቸውን ተናግረዋል። በያዮ ወረዳ የአጪቦ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ጌታቸው በቀለ፣ አርሶ አደር ተስፋዬ ሀብተማርያም እና አርሶ አደር ብርሃኔ አሰፋ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በኩታ ገጠም ከ116 ሔክታር በላይ መሬት ላይ በቆሎ መዝራት መጀመራቸውን ገልጸዋል። አርሶ አደሮቹ የማሳ ዝግጅት ስራቸውን ቀደም ብለው በማከናወናቸው እንዲሁም የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ አቅርቦትም ቀድሞ በመድረሱ ማሳቸውን በዘር የመሸፈን ተግባርን ቀድመው መጀመራቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም የግብርና ስራቸውን በቴክኖሎጂ ለመደገፍ በትራክተር የማረስ ስራ እንዲያከናውኑ በወረዳው አስተዳደር በኩል አስፈላጊው እገዛ እንደተደረገላቸውም ገልጸዋል።  
ለዒድ አል-አድሃ (ዓረፋ) በዓል የምርት እጥረት እንዳያጋጥም ዝግጅት ተደርጓል-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 25, 2026 197
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ በመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች ዘንድ ለ1447ኛ ጊዜ የሚከበረውን የዒድ አል-አድሃ (ዓረፋ) በዓል ምክንያት በማድረግ ነዋሪዎቻችን በዓሉን ያለምንም የገበያ ጫና እና እንግልት በደስታ ማክበር እንዲችሉ፣ መሰረታዊ የፍጆታ ዕቃዎች እና የበዓል ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እና በበቂ መጠን እንዲቀርቡ ሰፊ ዝግጅት መደረጉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።   በተለይም በከተማችን በሚገኙ 7ቱም የግብርና ምርቶች መሸጫ ማዕከላት የሰብል፣ የጥራጥሬ፣ የአትክልትና የፍራፍሬ ምርቶች በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ ቀርበው ይገኛሉ ብለዋል። ሸማቾች በቀላሉ በአቅራቢያቸው መገብየት እንዲችሉ በሁሉም አካባቢዎች የሚገኙ 250 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች እስከ በዓሉ ዋዜማ ድረስ ክፍት ሆነው እንዲሰሩ ተደርጓል።   በ2 ሺህ 52 የሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት ሱቆች እና በአዲስ አበባ ንግድ ስራዎች ድርጅት መጋዘኖች አማካኝነት የዘይት እና የዱቄት ምርቶች በበቂ መጠን ተደራሽ ሆነዋል።   በመሆኑም የከተማችን ነዋሪዎች ከተጠቀሱት የገበያ አማራጮች በአቅራቢያችሁ ከሚገኙት መጠቀም ትችላላችሁ ሲሉ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ጠቁመዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ የሚያግዙ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተከናወነ ነው
May 25, 2026 281
ደሎ መና፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ የሚያግዙ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል የመስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ሮባ ቱርቼ አስታወቁ። በባሌ ዞን ደሎ መና ወረዳ ከ936 ሚሊየን ብር በሚልቅ ወጪ የተገነባው የያዶት የመስኖ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል። ፕሮጀክቱ የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ከመቀነስ ባለፈ፤ ለእንስሳት የመጠጥ ውኃ አገልግሎት የሚውል መሆኑም ተመላክቷል። አቶ ሮባ ቱርቼ በምረቃው ወቅት እንዳሉት፤ የክልሉ መንግሥት የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ትርጉም ባለው መልኩ ለመቀነስ የሚያግዙ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ ላይ በትኩረት እየሠራ ይገኛል። መንግሥት የአርብቶ አደሩ ማኅበረሰብ በተደጋጋሚ ጊዜ የሚያጋጥመውን ድርቅ እንዲቋቋም በክልል ደረጃ ከ166 የሚበልጡ ዘመናዊ የመስኖ ፕሮጀክቶችን አጠናቆ ለአገልግሎት አብቅቷል ብለዋል። ከተጠናቀቁት የመስኖ ፕሮጀክቶች መካከል 66 የሚሆኑት ለሰውና ለእንስሳት መጠጥ ጭምር አገልግሎት የሚውሉ መሆናቸውንም አስረድተዋል። በዛሬው ዕለት ለምረቃ የበቃው የያዶት የመስኖ ፕሮጀክት ከ3 ሺህ ሔክታር የሚበልጥ መሬት በማልማት ከ6 ሺህ በላይ አባወራዎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። የባሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሀኪም አልይ በበኩላቸው፤ በዞኑ ቆላማ አካባቢዎች የተገነቡ የመስኖ ፕሮጀክቶች የአርብቶ አደሩን ኑሮ በማሻሻል በኩል ከፍተኛ ውጤት እያመጡ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ ከ1 ሺህ 700 የሚበልጡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ከ4 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ ተገንብተው እየተመረቁ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይም ኅብረተሰቡን በቀጥታ ተጠቃሚ ለሚያደርጉ ፕሮጀክቶች ቅድሚያ እንደሚሰጥ አመላክተዋል። የክልሉ መንግሥት የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለሚያረጋግጡ የልማት ፕሮጀክቶች ልዩ ትኩረት መስጠቱን ያረጋገጡት ደግሞ በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ መንግሥቱ በቀለ (ዶ/ር) ናቸው። የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የቆላማና ዝናብ አጠር አካባቢዎች ዘላቂ ልማት ዕቅድ በመንደፍ የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቋቋም በትጋት እየተሠራ ነው ብለዋል። በቀጣይም የክልሉ መንግሥት ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ለውጤት በማብቃት የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገልጿል።
በክልሉ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የሕብረት ሥራ ማህበራትን የማብቃት ሥራው ይጠናከራል-እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
May 25, 2026 136
ሆሳዕና፣ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የሕብረት ሥራ ማህበራትን ደግፎ የማብቃት ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። ርዕሰ መስተዳድሩ በሀድያ ዞን ሊቻ ሁለገብ የገበሬዎች ሕብረት ሥራ ዩኒየን የወተት ማምረቻ፣ ማቀነባበሪያና ግብይት ማዕከልን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት፥ በክልሉ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የሕብረት ሥራ ማህበራትን ደግፎ የማብቃት ጅምሩ ተጠናክሮ ይቀጥላል።   በክልሉ የሕብረት ሥራ ማህበራት በምርጥ ዘርና በግብአት አቅርቦት ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩንና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማበርከት ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል። ዛሬ ለምረቃ የበቃው ሊቻ የሀድያ ገበሬዎች ሕብረት ሥራ ዩኒየን የወተት ማምረቻ፣ ማቀነባበሪያና ግብይት ማዕከል ከአርሶ አደሩ የሰበሰበውን የወተት ምርት እሴት ጨምሮ ለገበያ እንደሚያቀርብም አስረድተዋል። ዩኒየኑ የራሱን ገቢ ከማሳደግ ባለፈ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን ጠቅሰው፣ የክልሉ መንግስት ጠንካራ የሕብረት ሥራ ማህበራትን ለማጠናከር የጀመረውን ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኡስማን ስሩር በበኩላቸው፥ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ የሆነው የሌማት ትሩፋት ትግበራ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ከጊዜ ወደ እያሳደገው ነው። በክልሉ በግብርናው ዘርፍ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ከቤተሰብ አልፎ በማህበረሰብ ደረጃ ለማረጋገጥ የተጀመረው ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው የገለፁት። ሊቻ የሀድያ ገበሬዎች ሁለገብ ዩኒየን ሥራ አስኪያጅ አቶ ኤርሚያስ ሽፈራው እንደገለጹት፥ ዩኒየኑ የግብርና ግብዓት አቅርቦትን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች ላይ እየሰራ ይገኛል። ዩኒየኑ 85 ሺህ የሚጠጋ አባላት እንዳሉትና ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገቡን ገልጸው፣ በልማት ስራዎቹም ከአባላቱ በተጨማሪ የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል።   ዛሬ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የወተት ማምረቻና ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ከአካባቢው አርሶ አደር ወተት በማሰባሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማህበረሰቡ ያቀርባል ብለዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልሉና የሀድያ ዞን ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የዩኒየኑ አባላት ተገኝተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በምዕራብ ጉጂ ዞን በመኸር እርሻ ከ339 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት ይለማል
May 25, 2026 115
ነጌሌ ቦረና፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፡- በዘንድሮው የመኸር እርሻ የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ከ339 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት ለማልማት ሥራ መጀመሩን የምዕራብ ጉጂ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። ዞኑ በአምስት ዋና ዋና ሰብሎች በሚያከናውነው በዚህ የመኸር አዝመራ ከ8 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ማቀዱን የጽሕፈት ቤቱ የሰብል ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ ታሪኩ ብዙአየሁ ገልጸዋል። በዚህም መሠረት በዘጠኝ ወረዳዎች 339 ሺህ ሔክታር እንደሚለማና በልማት ሥራውም ከ293 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮች እተሳተፉ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። እስካሁን ባለው እንቅስቃሴም በሁሉም የዞኑ ወረዳዎች የመጀመሪያ ዙር የእርሻ ሥራ መጠናቀቁን አረጋግጠዋል። በመኸር አዝመራው በስፋት ስንዴ፣ ጤፍ፣ በቆሎ፣ ቦለቄና ማሾ እንደሚለማ ገልጸው፤ ምርታማነትን ለማሳደግ የተለያዩ ስልቶች ተግባራዊ ይደረጋሉ ብለዋል። ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በበቂ ሁኔታ እንዲቀርብ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው፤ የግብርና ሥራውም በትራክተር፣ በመስመርና በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ እየተካሄደ መሆኑን አስረድተዋል።
የሥራ ገበያ ምኅዳሩን በዲጂታል ሥርዓት በማዘመን ሥራና ሰራተኛ በቀላሉ የሚገናኝበት ዕድል እየተፈጠረ ነው
May 25, 2026 429
አዲስ አበባ፤ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦የሥራ ገበያ ምኅዳሩን በውጤታማ የዲጂታል ሥርዓት በማዘመን ሥራና ሰራተኛ በቀላሉ የሚገናኝበት ዕድል እየተፈጠረ መሆኑን የሥራ ክህሎት ሚኒስትር ሙፈርያት ካሚል ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ጋር በመተባበር ያለማውን ሥራና ሰራተኛ በቀላሉ የሚገናኝበት 'ፈልጉልኝ' የተሰኘ ዘመናዊ የዲጂታል መተግበሪያ ይፋ አድርጓል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈርያት ካሚል በዚሁ ወቅት፤ የዜጎችን የሥራ ዕድል ፈጠራ የሚያዘምኑ የዲጂታል አማራጭ የማሻሻያ እርምጃዎች ተግባራዊ እየተደረጉ ነው ብለዋል። ይፋ የተደረገው 'ፈልጉልኝ' የሥራና ሰራተኛ አገናኝ መተግበሪያም ሥራና ሰራተኛን በቀላሉ የሚያገናኝ የዲጂታል አማራጭ መሆኑን ገልጸዋል። ሥራና ሰራተኛ በዲጂታል ሥርዓት የሚገናኝበት መተግበሪያም በሁሉም ዘርፍ ሙያና ክህሎት ያላቸው ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያሰፋ እንደሆነ ተናግረዋል። መተግበሪያውን ከፋይዳና የኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሰርዓት ጋር በማስተሳሰር በተለያዩ የቋንቋ አማራጮች ተደራሸ የማድረግ ዕድል መፈጠሩን አስረድተዋል። በመተግበሪያው የተካተቱ የተሟላና አስተማማኝ የቴክኖሎጂ አማራጮች ፍትሐዊ የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ምኅዳርን በመፍጠር የማይተካ ሚና እንዳለው አንስተዋል። የሥራ ገበያ ምኅዳሩን በውጤታማ የዲጂታል ሥርዓት በማዘመን ሥራና ሰራተኛ በቀላሉ የሚገናኝበት ዕድል እየተፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ፤ መተግበሪያው በሀገር በቀል የቴክኖሎጂ ዕውቀት የለማና ደህንነቱ የተጠበቀ ነው ብለዋል። ይህም የመረጃ ሉዓላዊነትና ደህንነትን ለማስጠበቅ ተደማሪ አቅም እንዳለው ገልጸዋል። አምስት የሀገር ዉሰጥ ቋንቋዎችና አጭር የስልክ መልዕክት አማራጭ በመተግበሪያው መካተታቸውም የዜጎች ተጠቃሚነትን ለማላቅ ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይልን በመጠቀም በአፍሪካ ወደ አረንጓዴ ትራንስፖርት ለሚደረገው ሽግግር ግንባር ቀደም ሆና እየሰራች ነው
May 25, 2026 165
አዲስ አበባ፤ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የታዳሽ ኃይል ምንጭ በመጠቀም በአፍሪካ ወደ ንጹህና አረንጓዴ ትራንስፖርት የሚደረገውን ሽግግር በግንባር ቀደምትነት ለመምራት እየሰራች መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያን የትራንስፖርት ዘርፍ ወደ አረንጓዴ፣ዘላቂ እና አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ (ኢ-ሞቢሊቲ) ሥርዓት የሚያሸጋግር ብሄራዊ የኢ-ሞቢሊቲ ስትራቴጂና የትግበራ እቅድ ይፋ ማድረጊያ መርሃግብር እየተካሄደ ይገኛል። በመርሃግብሩ ላይ ከተለያዩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች የተወከሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ተወካዮችና የልማት አጋሮች ተገኝተዋል። የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) እንዳሉት፥ አዲሱ ስትራቴጂ የሀገሪቱን የትራንስፖርት ዘርፍ በዘመናዊ መልክ ለመቅረጽ የሚጠቅም ነው ብለዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ ንጹህ ከተሞችን መፍጠር እና የህዝብ ጤናን ማሻሻል፣ ለነዳጅ ግዢ የሚወጣውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ መቆጠብ፣ የሀገሪቱን የኃይል ደህንነት ማረጋገጥ የሚያስችል ምህዳርን መገንባት እንደሚረዳም ተናግረዋል፡፡ ይህ ስትራቴጂ የፖሊሲ እና የህግ ማሻሻያዎችን፣ የኃይል መሙያ ጣቢያዎች ግንባታን፣የህዝብ ትራንስፖርትን በኤሌክትሪክ መተካትን፣ የሀገር ውስጥ ምርትን ማሳደግና የግል ባለሀብቶችን ተሳትፎ ማሳደግን ያካተተ ግልጽ ፍኖተ-ካርታ የያዘ ነው ብለዋል። የኢ-ሞቢሊቲ ሽግግር የአንድ ተቋም ብቻ ኃላፊነት ሳይሆን የጋራ ሀገራዊ ጥረትን የሚጠይቅ መሆኑን ጠቁመው፤ የመንግስት ተቋማትን ጨምሮ የግሉ ዘርፍም ኢንቨስትመንትን እንዲያሳድጉና መሰረተ-ልማቶችን እንዲያስፋፉ ጥሪ አቅርበዋል።   የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል በበኩላቸው፥ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የትራንስፖርት ወጪንና በነዳጅ ላይ ያለንን ጥገኝነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚቀንሱ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ገበያ የካርቦን ልቀትን መመዝገብ አስገዳጅ እየሆነ በመምጣቱ፣ አረንጓዴ ልማት ለአካባቢ ጥበቃ ብቻ ሳይሆን በገበያ ውስጥ በዘላቂነት ለመቆየት ወሳኝ መስፈርት መሆኑን አብራርተዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የሀገር ውስጥ ምርትና መገጣጠምን በማሳደግ በ2030 የሀገር ውስጥ ምርት ድርሻን ሰላሳ በመቶ ለማድረስ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በቀጣይ የባትሪ ስነ-ምህዳር እና ሰርኩላር ኢኮኖሚ መዘርጋት፣የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቴክኖሎጂ እና ኢንዱስትሪ ፓርኮችን መገንባት፣ ጥራትን ለመጠበቅ አስገዳጅ የሆኑ ብሄራዊ ደረጃዎችን መተግበር እንዲሁም ለባትሪ ምርት ወሳኝ የሆኑትን ማዕድናት ክምችት ጥናት ማፍጠን የትኩረት አቅጣጫዎች ናቸው ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በርካታ ኢንቨስተሮች በኢትዮጵያ ያሉ ማዕድናትን ተጠቅመው በሊቲየም ባትሪ ማምረቻ ዘርፍ ለመሰማራት ፍላጎት እያሳዩ መሆኑን ጠቅሰው፤ የግሉ ዘርፍ በተዘጋጁት ማበረታቻዎችና የቴክኖሎጂ ፓርኮች በመጠቀም በዘርፉ እንዲሰማራ ጥሪ አቅርበዋል። በተጨማሪም ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋር በመሆን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ የልህቀት ማዕከላትን ለማቋቋም እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።   በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የቴክኖሎጂ፣ ኢኖቬሽንና መሰረተ-ልማት ልማት ዲቪዢን ዳይሬክተር ሮበርት ሊሲንጌ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በዓለም አቀፍና በአፍሪካ ደረጃ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች አጠቃቀም በፍጥነት እያደገ መሆኑንና ኢትዮጵያም በዚህ የሽግግር ሂደት ውስጥ በግንባር ቀደምትነት እየመራች መሆኑን አረጋግጠዋል። ይህ የኢ-ሞቢሊቲ ሽግግር ከልቀት ነፃ የሆኑ ከተሞችን ከመፍጠር ባለፈ፣በነዳጅ ምርቶች ሳቢያ የሚወጣውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ በማስቀረት ለኢኮኖሚው ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የአባል ሀገራትን የኢ-ሞቢሊቲ ጉዞ ለመደገፍ ከአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና ከተባበሩት መንግስታት የአካባቢ ጥበቃ ፕሮግራም ጋር በመሆን የአፍሪካን የኢ-ሞቢሊቲ አህጉራዊ ማዕቀፍ አዘጋጅቶ እንዲፀድቅ ማድረጉን አስታውቀዋል። ይህንን አህጉራዊ ማዕቀፍ ወደ ሀገራዊ ተግባር ለመለወጥ የሚያስችል ፍኖተ-ካርታ መዘጋጀቱንና የ2026 የአፍሪካ ኢኮኖሚ ሪፖርትም የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በምጣኔ ሀብት ሽግግር ላይ ያላቸውን ተፅዕኖ በጥናት መተንተኑን ጠቁመው፣ ኮሚሽኑ የኢትዮጵያን የኢ-ሞቢሊቲ ሽግግር ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን በድጋሚ አረጋግጠዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በክልሉ የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ ነው
May 24, 2026 424
ነገሌ ቦረና፣ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ መሆናቸው ተገለጸ። በምስራቅ ቦረና ዞን ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ የተገነቡ የፊና መስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀዋል፡፡   ፕሮጀክቶቹን የመረቁት በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት በምክትል ርእሰ መስተዳድር ማእረግ የማህበራዊ ዘርፍ ክላስተር አስተባባሪ አቶ ሳዳት ነሻህ ናቸው፡፡ የክልሉ መንግስት የአርብቶ አደሩን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የቆላማና ዝናብ አጠር አካባቢዎች ዘላቂ ልማት እቅድ በመንደፍ የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቋቋም እየሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብርን የማጠናከር፣ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራና የበጋ መስኖ ልማትን በመተግበር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ መሰራቱን አንስተዋል። በክልሉ የቆላማ አከባቢዎች የአርብቶ አደሩን የመስኖ ልማትን ለማጠናከርና የእንስሳት መጠጥ ወሀ አቅርቦት ችግር ለመፍታት የፊና ፕሮጀክቶችን እውን ለማድረግም ጥረት መደረጉን ገልጸዋል፡፡ በምስራቅ ቦረና ዞን ዛሬ ለምርቃት የበቁት ፕሮጀክቶችም የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ለማሳካትና ለእንስሳት ውሀ አቅርቦት ይውላሉ ብለዋል፡፡ በቀጣይም የክልሉ መንግስት ተመሳሳይ ፕሮጀክቶችን ለውጤት በማብቃት የአርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የሚያደረገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል፡፡ የክልሉ መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ምክትል ሀላፊ ኢንጅነር አለሙ ረጋሳ በምስራቅ ቦረና ዞን የአርብቶ አደሩን የመሰረተ ልማት ተደራሽነት ለማረጋገጥ በግንባታ ላይ ከነበሩ ሶስት የፊና መስኖ ፕሮጀክቶች መካከል ሁለቱ ለአገልግሎት መብቃታቸውን ጠቁመዋል። በዞኑ ሊበንና ጎሮ ዶላ ወረዳ በግንባታ ላይ ከነበሩት ሁለቱ ሙሉ በሙሉ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹም በቆላማና ዝናብ አጠር አከባቢዎች የሚታየውን የድርቅ ተጋላጭነት በዘላቂነት ለመቋቋም፣ ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማትና ለእንስሳት መጠጥ ውሀ አቅርቦት እንዲሁም ለመኖ ልማት እንደሚውሉ አመላክተዋል። የክልሉ መንግስት ግንባታቸው ለተጠናቀቁት የፊና መስኖ ፕሮጀክቶች 518 ሚሊዮን ብር ወጭ ማድረጉን አስታውቀዋል፡፡ የመስኖ ፕሮጀክቶቹ 8 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሜትር ኪውብ የዝናብ ውሀ የመያዝ አቅም ያላቸው እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡ የምስራቅ ቦረና ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱረዛቅ ሁሴን በበኩላቸው ፕሮጀክቶቹ ከ465 ሄክታር በላይ መሬት በመስኖ የማልማት አቅም አላቸው ብለዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹ አርብቶ አደሩን በመስኖ ልማት በመሰማራት ተጠቃሚ ከማድረግ ባሻገር ከቀየው ሳይርቅ ለእንስሳቱ የመጠጥ ውሀ እንዲያገኝ የሚያስችሉት መሆኑን አመልክተዋል። በዞኑ የሊበን ወረዳ ነዋሪ አቶ ቃሲም ገመዳ በበኩላቸው የፕሮጀክቶቹ መገንባት የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጥያቄዎች የመለሱ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ በአካባቢው የተሰሩት የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎች ቀደም ሲል ለእንስሳት መኖና የመጠጥ ውሀ ፍለጋ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ እንደሚያስቀሩላቸው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም