ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ኢትዮጵያ ከብሔራዊ ልማት አጀንዳ ጋር የተቀናጀ አደጋን የመቋቋም አቅም እየገነባች ነው-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 9, 2026 147
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ ከብሔራዊ ልማት አጀንዳ ጋር የተቀናጀ አደጋን በራስ የመቋቋም አቅም በመገንባት ረገድ ለአፍሪካ የተግባር ምሳሌ መሆኗን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። 16ኛው የአፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም ጉባኤ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀመንበር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲና ሌሎች የጉባኤው ተሳታፊዎች በተገኙበት በአዲስ አበባ ተካሂዷል።   ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በጉባኤው ባደረጉት ንግግር የአየር ንብረት ለውጥ ጉዳት ቢጨምርም ዓለም አቀፋዊ ትብብርና መደጋገፍ እየላላ መጥቷል ብለዋል። በኢኮኖሚ እና የፖለቲካ ለውጦች ለሰብዓዊ ምላሽ የሚውል የድጋፍ ሀብት መቀነሱን አንስተዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አደጋ ጠንቅቃ ከመገንዘብ ባለፈ የጉዳቱ ገፈት ቀማሽ በመሆኗ የመቋቋም አቅምን የሚያጠክሩ እርምጃዎችን መውሰድ መጀመሯን ገልጸዋል። የረጅም ጊዜ ዝቅተኛ የካርቦን ልቀት እና የአየር ንብረት መቋቋም ልማት ስትራቴጂን በመቅረጽ ለሀገራዊ እድገት እና ለዓለም አቀፋዊ ምላሽ ያላትን ቁርጠኝነት ማሳየቷን ጠቅሰዋል። ሀገር በቀል ፖሊሲዎችን በሁሉም መስኮች በውጤታማነት እየተገበረች ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ከብሔራዊ የልማት አጀንዳዎች ጋር የተቀናጀ የአደጋ መቋቋም አቅም እየገነባች ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የምግብ ሉዓላዊነት፣ የኮሪደር ልማት፣ የታዳሽ ኃይል እና የሰብዓዊ ድጋፍ ሉዓላዊነት አደጋን በራስ አቅም የመቋቋምና በፈተና የማትበገር ሀገር የመገንባት ወሳኝ አምዶች መሆናቸውንም አስረድተዋል። ዘላቂ መጻኢ እድልን ለማረጋገጥ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥሩ በማንሳት፥ ከኢትዮጵያ አልፎ ፋይዳና ተሞክሮነታቸው ለአፍሪካ እንደሚተርፍ ገልጸዋል። ከዚህ አኳያ የአፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም አህጉሪቱ በሳይንስና በፈጠራ በመታገዝ በጋራ የመስራትና ችግሮችን የመቋቋም አቅምን የሚያሳይ ነው ብለዋል። ተቋሙ አፍሪካውያን ከአደጋ በኋላ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ለአደጋ ቀድሞ ወደ መዘጋጀት እንዲሸጋገሩ እያገዘ መሆኑን ጠቅሰው፥ በአጀንዳ 2063 ራሷን የቻለች፣ የማትበገርና የተባበረች አፍሪካን ለመገንባት ትልቅ አቅም መሆኑን ጠቅሰዋል። የመቋቋም አቅምን ለመገንባት በሀገራት፣ በተቋማት እና በዘርፎች መካከል ያለውን ትብብር፣ መተማመን፣ መደጋገፍና የጋራ አመራርን ማጠናከር እንደሚገባ አንስተዋል። ለዚህ ደግሞ አፍሪካ ግዙፍ አቅም፣ ሀብት፣ እውቀት እንዳላት ገልጸው፥ የሚያስፈልገን በአንድነት እና በዓላማ መነሳት ብቻ ነው ብለዋል። ከአደጋ ስጋት ወደ አይበገሬነት የሚደረገው ጉዞ ራዕይን፣ ቁርጠኝነትን እና ቀጣይነት ያለው እርምጃን እንደሚጠይቅም አንስተዋል። የአፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም የአፍሪካ የአንድነትና የሉዓላዊነት ምሰሶ በመሆኑ የያዘው ግብ እንዲሳካ የፖለቲካ ቁርጠኝነት፣ ዘላቂ ፋይናንስ እና ጠንካራ ቴክኒካዊ አቅም እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።    
የአፍሪካን ችግሮች በአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት ለመፍታት ሀገራት ትብብራቸውን ሊያጠናክሩ ይገባል
Apr 9, 2026 149
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡- የአፍሪካን ችግሮች በአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት በመፍታት ከውጭ ጥገኝነት ለማውጣት ሀገራት ትብብራቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊክ ሀዳዲ ገለጹ። ኢትዮጵያ የምታስተናግደው16ኛው የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አህጉራዊ ጉባኤ "ለሉዓላዊነት መተባበር" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን እየተካሄደ ነው።   የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አባል ሀገራትና ታዛቢዎች እንዲሁም የዘርፉ ተዋንያን የሚሳተፉበት ጉባኤው በአፍሪካውያን መካከል ትብብርና አጋርነትን በመፍጠር አህጉራዊ የአደጋ ሥጋትን የመከላከልና የፋይናንስ አቅምን ማጠናከርን ያለመ ነው። ጉባኤው የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም፣ ለአደጋ ስጋት ምላሽ ለመስጠት እና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ አፍሪካ መር መፍትሔ ማፈላለግ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ምክክርና የጋራ መግባባት መፍጠር ያስችላል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊክ ሀዳዲ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የአፍሪካ ሕብረት አባል ሀገራት እንደ አፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም ያሉ ተቋማት ጋር በጋራ መስራት አለባቸው። በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያመጣው ማህበራዊ፣ ኢኮናሚያዊና የስነ-ምህዳር ለውጥ ጊዜ የሚሰጠው አይደለም ብለዋል። አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ያላት ድርሻ ከአራት በመቶ በታች ቢሆንም አምስት በመቶ ጥቅል አህጉራዊ ሀብቷን እያሳጣት መሆኑን ገልጸዋል። አሕጉራዊ ችግሮች አህጉራዊ መፍትሔ እንደሚሹ ገልጸው፤ የአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት ለአፍሪካ ችግሮች ቅድሚያ መስጠት አለባቸው ብለዋል። አሕጉራዊ ማዕቀፎችና ፖሊሲዎች ከዚህ ጋር መጣጣም እንዳለባቸው ጠቅሰው፤ ችግሩን በዘላቂነት በራስ አቅም ለመፍታት በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀጣይነት ያለው የፋይናንስ ስርዓት መዘርጋት ይገባል ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በአፍሪካ ሕብረት አባል ሀገራት መካከል ያለው ትብብር በማሳደግ የፋይናንስ አቅም ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። ከተናጠል እርምጃ ይልቅ በአባል ሀገራት መካከል ትብብርን ማጠናከርና ወደ ተግባር መቀየር ይገባል ያሉት ምክትል ሊቀ መንበሯ፤ አህጉራዊ የትኩረት መስኮች ላይ መተባበር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። አፍሪካ ከውጭ በሚመጣ ፋይናንስ ጥገኛ መሆን እንደሌለባት ጠቅሰው፤ ለአፍሪካ መፍትሔ ሀገር በቀል ዕውቀትና ቴክኖሎጂ ቅድሚያ መስጠት ይገባል ብለዋል። ግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት አካታችነት የምርጫ ጉዳይ አይደለም ያሉት ምክትል ሊቀ መንበሯ፤ ሴቶች፣ አካል ጉዳተኞችና ሁሉንም የማህበረሰብ ክፍሎች ማሳተፍ እንደሚገባ ገልጸዋል።
ለትንሳኤ በዓል የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኘን ነው- ሸማቾች
Apr 9, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018(ኢዜአ)፡- በመዲናዋ ለትንሳኤ በዓል የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኙ መሆኑን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ሸማቾች ገለጹ። ኢዜአ ለበዓል ፍጆታ የሚያስፈልጉ ልዩ ልዩ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች አቅርቦት ምን እንደሚመስል የህብረት ስራ ዩኒየኖችና ሸማች ህብረት ስራ ማህበራት የመሸጫ ሱቆች እና መደብሮች ቅኝት አድርጓል፡፡ ቅኝት ባደረገባቸው የሸማች ህብረት ስራ ማህበራትና ዩኒየኖች ለበዓል ፍጆታ የሚያስፈልጉ ምርቶች ማቅረባቸውንና ህብረተሰቡም ሲገበያይ መመልከት ችሏል። የብርሃን ለሸማቾች ህብረት ስራ ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ ይታየው ታደለ ለኢዜአ እንደገለጹት ለትንሳኤ በዓል ተፈላጊ የሆኑ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች ለማቅረብ ቀደም ተብሎ ዝግጅት ሲደረግ ቆይቷል። ከአምራቾች ጋር ትስሰር በመፍጠርና በዩንዮኖች በኩል ያለ ደላላ ጣልቃ ገብነት በቂ ምርት ወደ ህብረት ስራ ማሀበራት ማስገባት መቻሉን አስታውቀዋል፡፡ ይህን ተከትሎ ለትንሳኤ በዓል ዘይት ዱቄት፤ ሽንኩርት ፤እንቁላል እና ሌሎችም ለበዓሉ አስፈላጊ የሆኑ ምርቶችን በስፋት እና በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል፡፡   አውቶቡስ ተራ ሁለገብ ሸማች ሃላፊነቱ የተወሰነ ህብረት ስራ ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ አንዷለም አስማረ በበኩላቸው፤ ለበዓሉ አስፈላጊ የሆኑ የባልትና ውጤቶችን ጨምሮ ሌሎችን ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እየተከፋፈለ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የብስራት ለጉለሌ ዩኒየን ዋና ስራ አስኪያጅ ሞገስ መንገሻ በዩኒየኑ ባሉት 10 መሰረታዊ ህብረት ስራ ማህበራት በኩል ምርቶቹን ለመሰረታዊ ማህበራትና ለህብረት ስራ ማህበራቱ በጅምላ እየተከፋፈለ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   በማህበራቱ ሲሸምቱ ያገኘናቸው ሸማቾች በበኩላቸው፤ ለበዓሉ ተፈላጊ የሆኑ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል።   ካነጋርናቸው ሸማቾች መካከል ወይዘሮ ዓለም ለገሰ እንዳሉት ከዘይት ጀምሮ ለበዓል ተፈላጊ የሚባሉ ሽንኩርትና የተለያዩ ግብዓቶች በተመጣጠነ ዋጋ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ ሌላኛዋ ሸማች ወይዘሮ ጤና ይበልጣል በበኩላቸው በሸማቾች በኩል ለበዓሉ የሚያስፈልጉ የተለያዩ ምርቶችን ማግኘታቸውን አንስተዋል፡፡   መንግሥት በህብረት ሥራ ማህበራት አማካኝነት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ የገበያ መረጋጋት ለመፍጠር ያከናወናቸው ተግባራት የሚደነቁ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ወይዘሮ ፍሬህይወት አባይነህ እና ብዙአየሁ አበበ ናቸው፡፡      
የምስራቅ ቦረና ዞን የነዳጅና የግብርና ምርቶችን በህገወጥ መንገድ የሚያዘዋውሩ አካላትን የመቆጣጠር ተግባሩን አጠናክሯል
Apr 9, 2026 91
ነገሌ ቦረና፤ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡- የምስራቅ ቦረና ዞን የነዳጅና የግብርና ምርቶችን በህገወጥ መንገድ የሚያዘዋውሩ አካላትን የመቆጣጠር ተግባር ማጠናከሩን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በህገወጥ የነዳጅና የግብርና ምርቶች ዝውውር ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በነገሌ ቦረና ከተማ ተካሄዷል፡፡ በዚሁ ወቅት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱረዛቅ ሁሴን፤ በዞኑ የሚገኙ አንዳንድ ነጋዴዎች በአቋራጭ ለመበልጸግ ምርት በመደበቅ ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ እያደረጉ ይገኛሉ። በተለይም ወቅታዊ ሁኔታውን ምክንያት በማድረግ በህገወጥ መልኩ ነዳጅን የሚያዘዋውሩ አካላት መኖራቸውም ተረጋግጧል ብለዋል። ለዚህም የዞኑ አስተዳደር ግብረ ኃይል አቋቁሞ ከማደያ ውጭ ነዳጅ በሚሸጡ ህገወጦች ላይ ጠንካራ ክትትልና ቁጥጥር እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በተደረገው ጥረትም በርካታ የንግድ ድርጅቶች መታሸጋቸውን፣ የተወሰኑ የንግድ ቤቶች ባለቤቶችም በቁጥጥር ስር ውለው ተጠያቂ መሆናቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም ህብረተሰቡ ያልተገባ የንግድ እንቅስቃሴ እንዲሁም ህገወጥ የምርት እና የሸቀጦች ዝውውር ሲመለከት ለሚመለከተው አካል ጥቆማ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርበዋል። በሌላ በኩል በንግዱ ማህበረሰብ ላይ ያልተገባ ድርጊት ሲፈጽሙ የተገኙ የመንግስት ሰራተኞችም ተጠያቂ እየተደረጉ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዞኑ ንግድ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ገልማ ገልገሎ፤ ህገወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመከላከል ከዞን አስተዳደር፣ ከንግድ፣ ከአቃቤ ህግ፣ ከፖሊስና ከሌሎችም ተቋማት የተውጣጣ የክትትልና ቁጥጥር ኮሚቴ ተቋቁሞ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል ብለዋል። ምርት የደበቁ፣ ፍትሀዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ ባደረጉና በኮንትሮባንድ ስራ ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎች ላይ ህጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም 177 ሚሊዮን ብር ግምት ያለው የኮንትሮባንድ እቃ ሲያዘዋውሩ የተገኙ 62 ግለሰቦች ፍርድ ቤት መቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ በሀገር ውስጥ ምርቶች ላይ ፍትሀዊ ያልሆነ ዋጋ በሚጨምሩ የንግድ ድርጅቶች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል።   የነዳጅ ምርት በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ቅድሚያ ማግኘት የሚገባቸው አካላት እንዲያገኙ ጥብቅ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑንም አስረድተዋል።   በውይይት መድረኩ ላይ የተሳተፉት የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪው አቶ ግዛቸው ካሳ፤ በህገወጦች ላይ የተጀመረው ክትትልና ቁጥጥር ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል።   ሌላዋ የመድረኩ ተሳታፊ ወይዘሮ አይናለም አየለ በበኩላቸው፤ የዞኑ አስተዳደር ህገወጥነት ላይ የጀመረው ቁጥጥር ውጤታማ እንዲሆን የበኩላቸውን እንደሚወጡም አረጋግጠዋል።    
በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በህገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የተገኘ 12 በርሜል ነዳጅ በቁጥጥር ስር ዋለ
Apr 9, 2026 85
ገንዳውኃ፣ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በህገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የተገኘ 12 በርሜል ነዳጅ በቁጥጥር ስር ማዋሉን የወረዳው ፖሊስ አስታወቀ። በመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት ምክንያት የተከሰተውን የነዳጅ አቅርቦት ችግር ለመቋቋም በመንግስት በኩል ግብረ ሃይል ተቋቁሞ የተለያዩ የመፍትሄ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑ ይታወቃል። የነዳጅን አጠቃቀምን በቁጠባ ከማድረግ በተጓዳኝ የነዳጅን ግብይት ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴን መቆጣጠርና ጥብቅ ክትትል ማድረግ እንደሚገባም ተመላክቷል። በዚህም መሰረት በአማራ ክልል በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በህገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የተገኘ 12 በርሜል ነዳጅ በቁጥጥር ስር ማዋሉን የወረዳው ፖሊስ አስታውቋል። በወረዳው ፖሊስ ጽህፈት ቤት የወንጀል ምርመራ ክፍል ኃላፊ ኢንስፔክተር ፍቅሩ አባይ፤ በህገ ወጥ መልኩ ተከማችቶ የተገኘው ነዳጅ በገለጉ ከተማ በሁለት ግለሰቦች በመኖሪያ ቤት መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም በህዝብ ጥቆማ በተደረገው ክትትል የነዳጅ ምርቱን ከነተጠርጣሪ ግለሰቦቹ ፖሊስ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገልጸዋል። ግለሰቦቹ በህገ ወጥ መንገድ ለመክበር በመፈለግ በሀገርና በህዝብ ላይ ጉዳት ለማድረስ የፈጸሙት መሆኑን አንስተው በቀጣይም ጥብቅ ቁጥጥር የማድረግና ተጠርጣሪዎችን በህግ ተጠያቂ የማድረግ ስራ ይቀጥላል ብለዋል።  
በጉራጌ ዞን በዓልን ተከትሎ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይደረግ ቁጥጥር እየተደረገ ነው
Apr 9, 2026 93
ወልቂጤ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በጉራጌ ዞን በዓልን ተከትሎ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይደረግ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ገለጸ። የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ በዞኑ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን በማጠናከር የፍጆታ ምርቶች ለሸማቾች በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረቡ መሆናቸው ተመላክቷል። የጉራጌ ዞን ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ መኩሪያ ተመስገን እንደገለጹት፤ የትንሳኤ በዓልን ተከትሎ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይከሰት በትኩረት እየተሰራ ነው። ለዚህም በመንግስት እና በግል የንግድ ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት እየተሰራ ባለው ተግባር የእርድ እንስሳት፣ ዘይት፣ ስኳር፣ የዳቦ ዱቄትና ሌሎች መሰረታዊ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን በበቂ ሁኔታ ማቅረብ መቻሉን ጠቁመዋል። በዞኑ የተቋቋሙ ከ37 በላይ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ዘወትር ጭምር አገልግሎት እንዲሰጡ በማድረግ በበቂ ሁኔታ ምርት እንዲቀርብ የማድረግ ስራ መከናወኑን አስረድተዋል። ከነዳጅ እጥረት የተነሳ የምርት አቅርቦት እንዳይስተጓጎል በዘርፉ ለተሰማሩ አሽከርካሪዎች ነዳጅ ቅድሚያ እንዲያገኙ በማድረግ የግብርናና የፋብሪካ ምርት እንዲቀርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን አጠናክሮ ከማስቀጠል ባለፈ ሳምንቱን ሙሉ አገልግሎት በመስጠት ለሸማቹ ማህበረሰብ የተለያዩ የአትክልት ምርቶች እየቀረቡ መሆኑን የሚናገሩት በወልቂጤ ከተማ በአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ የተሰማሩት ወይዘሮ ዘይነባ አወል ናቸው። ለበዓል የሚሆን በቂ ምርት ማቅረባቸውን አስረድተው በተመጣጣኝ ዋጋ እየሸጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በከተማው ሲገበያዩ ያገኘናቸው አቶ አስማማው ገብረማርያም በሰጡት አስተያየት፤ የእርድ እንስሳት፣ እንቁላልና አንዳንድ ለበዓል የሚያስፈልጉ ምርቶች ዋጋ ካለፉት ዓመታት መጠነኛ ጭማሪ ቢኖረውም የተሻለ አቅርቦት መኖሩን ገልጸዋል። የምርት አቅርቦቱ እና ገበያ ለማረጋጋት የተሰራው ስራ ሸማቹ በአቅሙ ልክ የሚፈልገውን ገዝቶ በዓሉን በደስታ ለማሳለፍ የሚያስችል ነው ብለዋል። በዓልን ምክንያት በማድረግ የቀረቡ የግብርና ምርቶች አምራቹ በቀጥታ ከማሳው ወደ ተጠቃሚው እንዲቀርብ ለማድረግ ጥረት መደረጉ ማሳያ ናቸው ያሉት ደግሞ ሌላኛው ሸማች አቶ ታረቀኝ ሀብቴ ናቸው። ለበዓሉ የሚሆኑ መሰረታዊ የፍጆታ ምርቶች ለሸማቹ በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውን በመግለጽ፣ በአንዳንድ ምርቶች ላይ አምና ከነበረው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የተወሰነ ጭማሪ መኖሩን ተናግረዋል።  
በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች ለትንሳኤ በዓል የሚያስፈልጉ ምርቶች በተሻለ ሁኔታ ቀርበዋል
Apr 9, 2026 148
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018(ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች ለትንሳኤ በዓል የሚያስፈልጉ ምርቶች በተሻለ ሁኔታ መቅረባቸውን ሻጮችና ሸማቾች ተናገሩ። የጅማ ከተማ ነዋሪው አቶ ባህሩ ታረቀኝ ለበዓል ገበያው አስፈላጊ የኢንዱስትሪ እና የግብርና ምርቶች መቅረባቸውን ገልጸው፣ በልዩ የበዓል ገበያው ከመደበኛው ዋጋ ባነሰ እየሸመትን ነው ብለዋል።   ሌላኛዋ ነዋሪ ረድኤት አማረ ለበዓሉ አስፈላጊ የሆኑ ግብዓቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመቷን ትናገራለች። ከወቅታዊ ሁኔታዎች አንጻር ትልቅ ስጋት እንደነበራት ተናግራ፤ ነገር ግን እንደታሰበው ሳይሆን የተሻለ አቅርቦት በመኖሩ በበቂ መሸመቷን ገልጻለች።   መሰል የበዓል ገበያዎች ቀደም ብሎ ታቅደው መዘጋጀታቸው ለማህበረሰቡ የተሻለ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጅማ ከተማ ነዋሪዋ ወይዘሮ ፀሐይነሽ ካሳ ናቸው። እንደ ወይዘሮ ፀሐይነሽ ገለጻ ሽንኩርት በ90 ብር፣ቲማቲም በተመጣጣኝ ዋጋ መግዛታቸውን የገለጹ ሲሆን ዘይት ከመደበኛው ገበያ በ300 ብር ቅናሽ መግዛታቸውን ተናግረዋል። በሸገር ከተማም ለትንሳኤ በዓል የተለያዩ ምርቶችና ሸቀጦችን ያቀረቡ ነጋዴዎች የበዓል ገበያው የተሻለ አቅርቦት ያለበት መሆኑን ተናግረዋል። በመልካ ኖኖ ክፍለ ከተማ ለበዓሉ ምርቶችን እያቀረበ ያለው አቶ ኬር መሃመድ አሊ እንደተናገሩት፣ ለዘንድሮ የትንሳኤ በዓል ከነዳጅ ጋር ተያይዞ የመጓጓዣ ሁኔታ ፈታኝ ቢሆንም የአቅርቦት እጥረት የለም።   በተለይም ቀይና ነጭ ሽንኩርት፣ ቲማቲምና ሌሎች የግብርና ምርቶች ከአምናው በተሻለ መልኩ በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረብን ነው ብለዋል። በክፍለ ከተማው በማህበር ተደራጅተው የእንቁላል ምርት ለበዓሉ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑን የተናገረው ደግሞ ወጣት አማኑኤል ጫላ ነው። ሌላው የአትክልትና ፍራፍሬ አቅራቢ አቶ ግርማ በቀለ፣ ዘንድሮ ብዛት ያለው ምርት መኖሩን ጠቅሰው፣ በተለይም ለበዓል ፍጆታ የሚውሉ ምርቶችን የህብረተሰቡን ኪስ ባልጎዳ መልኩ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ ጥረት እያደረግን ነው ብለዋል። አሁን ላይ ያለው የገበያ ሁኔታ አስደሳች ነው ያሉት አቶ ግርማ፣ ህብረተሰቡም በተሻለ ሁኔታ ምርቱን እየተጠቀመ ይገኛል ብለዋል። የምስራቅ ሸዋ ዞን የህብረት ስራ ማስፋፊያ ኤጀንሲ በበኩሉ መጪውን የትንሳኤ በዓል ምክንያት በማድረግ በቂ የእርድ እንስሳትና እህል ለገበያ መቅረቡን ገልጿል። የዞኑ የህብረት ስራ ማስፋፊያ ኤጀንሲ ኃላፊ አቶ አስራት ጌቱ እንደገለጹት፣ በዞኑ የትንሳኤ በዓል ገበያ የተረጋጋ እንዲሆን ከሉሜ አዳማ፣ መቂ ባቱና ቦራ ደንበል ዩኒየኖች እንዲሁም ከመሰረታዊ ማህበራት ጋር በመተባበር በቂ ምርት እንዲቀርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። በተለይም ሸማቹ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን ቀጥታ ከሻጩ እንዲያገኝ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው፣ በሉሜ አዳማ የህብረት ስራ ዩኒየን በኩል የደለቡ በሬዎች ለገበያ መቅረባቸውን ገልጸዋል። በተመሳሳይ ጤፍ፣ የስንዴ ዱቄት፣ ሽንኩርትና ቲማቲም ለበዓል ገበያው በተመጣጣኝ ዋጋ መቅረባቸውን ጠቁመዋል።  
በደብረ ብርሀን ከተማ ለትንሳኤ በዓል የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች በበቂ ሁኔታ ቀርበዋል 
Apr 9, 2026 106
ደብረ ብርሃን፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦የትንሳኤ በዓልን በማስመልከት የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውን የደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። የሰሜን ሸዋ ዞን ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ በበኩሉ አምራቾች፣ አቅራቢዎችና የሕብረት ሥራ ማህበራትን በማስተባበር በተሰራው ሥራ ምርቶች በበቂ ሁኔታ ለማቅረብ መቻሉን አስታውቋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ነዋሪዎች መካከል የደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪ አቶ ጌታቸው በላይነህ እንደገለጹት፤ ለትንሳኤ በዓል የእርድ እንስሳትና ሌሎች የግብርና ምርቶች በብዛትና በአይነት በገበያው ቀርበዋል።   ይህም ሸማቹ በአቅሙ ልክ የሚፈልገውን ገዝቶ በዓሉን በተረጋጋና በደስታ ለማሳላፍ እንደሚያስችላቸው ተናግረዋል። ወይዘሮ ሰርካለም ገበያው በበኩላቸው በዛሬው እለት መካከለኛ ዶሮ 1ሺህ 400 ብር ከፍተኛው 1ሺህ 800 ብር እየተሸጠ መሆኑን ገልጸው በዓሉ እየቀረበ ሲመጣ ገበያው መረጋጋት እየታየበት መሆኑን ተናግረዋል። የሻምበል፣ ነዋይና ጓደኞቻቸው የዶሮ እርባታ ህብረት ሽርክና ማህበር አባል ወጣት ሻምበል መንግስቱ እንዳለው ለትንሳኤ በዓል ከ11 ሺህ በላይ እንቁላል ለገበያ ማቅረባቸውንና አንዱን በ16 ብር እየሸጡ መሆናቸውን ተናግሯል።   የሰሜን ሸዋ ዞን ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሀላፊ አቶ ዘውገ ንጉሴ እንደገለጹት፤ ለትንሳኤ በዓል አምራቹና ሸማቹ በቀጥታ የሚገናኙበት ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። በዚህም የእርድ እንስሳት፣ ዶሮና እንቁላልን ጨምሮ ሌሎች የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች የግብይት ሰንሰለቱ ባጠረ መንገድ ለሸማቹ ማህበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ መቅረባቸውን አስረድተዋል። ከተለያየ አካላት ጋር ትስስር በመፍጠር 81ሺህ ሊትር ዘይት፣ 12ሺህ ኩንታል ጤፍ፣ 2ሺህ ኩንታል ስኳር እንዲሁም ሽንኩርትና ሌሎች ለበዓሉ አስፈላጊ ምርቶች መቅረባቸውንም አመልክተዋል። በከተማው አዲስ በተገነባ የገበያ ማዕከል የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ እየተሸጡ መሆኑንም አስረድተዋል።
በጋምቤላ ለትንሳኤ በዓል የሚያስፈልጉ ምርቶችና የእርድ እንስሳት በበቂ ሁኔታ ቀርበዋል
Apr 9, 2026 153
ጋምቤላ ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል ለትንሳኤ በዓል በምርቶችና እርድ እንስሳት በቂ አቅርቦት መኖሩን የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ገለፀ። የትንሳኤ በዓልን በማስመልከት ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑንም ቢሮው አስታውቋል።   የቢሮ ኃላፊው አቶ ኮንግ ኡላንግ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ለትንሳኤ በዓል በሚያስፈልጉ ምርቶችና የእርድ እንስሳት እጥረት እንዳይከሰት አስፈላጊው ዝግጅት ሲደረግ ቆይቷል። በዚህም ለበዓሉ የሚያስፈልጉ ምርቶችና የእርድ እንስሳት በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውን ገልፀዋል።   የበዓል ገበያውም የተሳለጠና የህዝቡን የመሸመት አቅም ያገናዘበ እንዲሆን ቢሮው ግብረ ሃይል አቋቁሞ ቁጥጥርና ክትትል እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ከአከፋፋይና ከቸርቻሪ ነጋዴዎች ጋር በመወያየትና ጥናት በማድረግ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ እንዲቀርብ እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል፡ ምክንያታዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ እየተወሰደ እንደሚገኝ የቢሮ ኃላፊው አስታውቀዋል። የበዓል ግብይት ሲያከናውኑ ከነበሩ መካከል ወይዘሮ በለጠች አጂና በሰጡት አስተያየት ለበአል የሚያስፈልጉ ምርቶች በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውን ተናግረዋል።   የዘንድሮው የበዓል ገበያ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር በፍጆታ ምርቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ መታየቱን ጠቅሰዋል። በተለይም በዘይት፣ በሽንኩርት፣ በቲማቲም እና በሌሎችም ምርቶች እንዲሁም በእርድ እንስሳት ላይ የዋጋ ጭማሪ መታየቱን ለአብነት አንስተዋል።   በዘንድሮው የትንሳኤ በዓል የእርድ እንስሳት የተሻለ አቅርቦት መኖሩን የገለፁት ደግሞ በእርድ እንስሳት ንግድ ስራ ላይ የተሰማሩት አቶ ዘመኑ አረጋ ናቸው። በምርቶች ላይ መጠነኛ የዋጋ ጭማሪ መታየቱንም ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ማግኘት ለቀጣናው መረጋጋት ወሳኝ ነው
Apr 9, 2026 215
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ፍትሐዊና ለቀጣናው መረጋጋት ወሳኝ ነው ሲሉ የአውሮፓ ፓርላማ አባል ቲየሪ ማሪያኒ ገለፁ። በአራተኛው ዓመታዊ የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት የቀይ ባሕር እና የኤደን ባህረ ሰላጤ ውይይት ላይ የታደሙት የአውሮፓ ፓርላማ አባል ቲየሪ ማሪያኒ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከፍትሃዊነት ባለፈ ለዓለም አቀፍ ደህንነት ሚናው የጎላ ነው። እንደ ባብ ኤል-መንደብ ያሉ ጠባብ የባህር መተላለፊያዎች መዘጋት በአውሮፓ የነዳጅ እና የማዳበሪያ አቅርቦት ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እያሳደሩ ይገኛሉ ብለዋል። ኢትዮጵያ በዚህ ስትራቴጂካዊ ቀጣና ውስጥ የምትገኝ ቁልፍ ሀገር በመሆኗ ያላት ሚና ለዓለም አቀፍ የንግድ ልውውጥ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። በባህር ሕግ ስምምነት ላይ እያንዳንዱ ሀገር የባህር በር ሊኖረው እንደሚገባ በግልጽ መቀመጡንም አንስተዋል። አውሮፓ በቀጣናው ዘላቂ ሰላም እንዲኖር ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላት የገለጹት የአውሮፓ ፓርላማ አባል ቲየሪ ማሪያኒ፤ ለዚህም የኢትዮጵያ የባህር በር ማግኘት ወሳኝ ነው ብለዋል። ይህም ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለቀጣናው መረጋጋትና ለዓለም አቀፍ የንግድ መስመሮች ደህንነት ዋስትና እንደሚሆን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ በሕዝብ ብዛት ቀዳሚ ከሆኑ ሀገራት አንዷ እና የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ ሆና የባህር በር አልባ መሆኗ አመክንዮአዊ አይደለም ሲሉም ተናግረዋል።
የነዳጅ ስርጭትና አጠቃቀም ላይ የተቀመጠው አሰራር ከዚህ ቀደም ያጋጥሙ የነበሩ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን የቀረፈ ነው
Apr 9, 2026 84
ሃዋሳ ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦የነዳጅ ስርጭትና አጠቃቀም ላይ የተቀመጠው አሰራር ቀልጣፋ እና ከዚህ ቀደም ያጋጥሙ የነበሩ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን የቀረፈ መሆኑ ተመለከተ፡፡ በሀዋሳ ከተማ የነዳጅ ስርጭትና አጠቃቀም በተቀመጠው አሰራርና የመፍትሄ አቅጣጫ መሰረት እየተከናወነ መሆኑንም የከተማ አስተዳደሩ የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ አስታውቋል። በመካከለኛው ምስራቅ በተፈጠረው ግጭት ምክንያት በኢትዮጵያ የነዳጅ ግብይትና አቅርቦት ላይ የሚያጋጥመውን ችግር ለመሻገር መንግስት የመፍትሄ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል፡፡ የሃዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ አገና ኔቶ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ እንደ ሃገር ነዳጅን በቁጠባ በመጠቀም ፍትሀዊ ስርጭቱን ለማረጋገጥ ቅድሚያ ነዳጅ እንዲያገኙ ለተፈቀደላቸው ተሽከርካሪዎች በኩፓን እንዲገበያዩ ተደርጓል፡፡   የከተማ አስተዳደሩ ፍትሃዊ የነዳጅ ስርጭትና ቁጥጥር ለመተግበር ግብረ ሃይል አቋቁሞ ወደ ስራ መግባቱንም ጠቁመዋል፡፡ በዚህም ነዳጅ ለሚያመላልሱ ቦቴዎች፣ የኤክስፖርት ምርቶች ለጫኑ ካሚዮኖች፣ ለአምራች ኢንዱስትሪዎችና ለህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪዎች ቅድሚያ በመስጠት እንዲስተናገዱ መደረጉን ገልጸዋል፡፡ ግብረ ሃይሉ እጥረቱን ተከትሎ ነዳጅ ላልተገባ ተግባር እንዳይውል ባደረገው ክትትልና ቁጥጥር በ17 ተሸከርካሪዎች ላይ እርምጃ መውሰዱንም ተናግረዋል፡፡ የከተማ አስተዳደሩ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እያከናወነ ያለው ተግባር ውጤት እየታየበት እንደሆነም ምክትል ከንቲባው ተናግረዋል፡፡ በከተማው ነዳጅ የሚያቀርቡ ማደያዎችም የተቀመጠውን መመሪያ ተከትለው እየሰሩ በመሆናቸው ከዚህ ቀደም የነበሩ ሰልፎች አለመኖራቸውን ገልጸዋል፡፡ የሃበሻ ነዳጅ ማደያ ስራ አስኪያጅ አቶ አባይ በሪሁን በበኩላቸው ከመንግስት በወረደው የአሰራር መመሪያ መሰረት ቅድሚያ ለሚሰጣቸውና ከሚመለከተው አካል ኩፖን ይዘው ለመጡ ተሸከርካሪዎች ነዳጅ በፍጥነት ማስተናገዳቸውን ተናግረዋል፡፡   አሰራሩ ቀልጣፋና ከዚህ ቀደም ያጋጥሙ የነበሩ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን የቀረፈ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ነዳጅን በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ሲቀዱ ያገኘናቸው አሽከርካሪዎች እንዳሉት፤ አዲሱ አሰራር ከዚህ ቀደም በነዳጅ ማደያ ቆመው የሚያጠፉትን ጊዜ አስቀርቶላቸዋል፡፡   አሰራሩ ቀጣይነት እንዲኖረው ክትትሉ መጠናከር እንዳለበትና ያገኙትን ነዳጅ ቆጥበው በመጠቀም ያጋጠመውን የነዳጅ እጥረት ለመሻገር የበኩላቸውን እንደሚወጡም ገልጸዋል፡፡
የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት በትኩረት እየተሰራ ነው
Apr 9, 2026 98
ደብረ ማርቆስና ገንዳውኃ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃምና በምዕራብ ጎንደር ዞኖች የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን የዞኖቹ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያዎች ገለጹ። በዞኖቹ መጪውን የትንሳኤ በዓል አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት ለሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት ብድር ከማመቻቸት አንስቶ ጊዜያዊ የገበያ ቦታዎች እስከ ማዘጋጀት የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውም ተመላክቷል። በምስራቅ ጎጃም ዞን ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ተወካይ ሃላፊ አቶ መለሰ የተመኝ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የትንሳኤ በዓልን አስመልክቶ ያልተገባ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት በትኩረት እየተሰራ ነው። ለሸማቶች ህብረት ስራ ማህበራት ከ24 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር በመመደብና ለአቅራቢ ኢንተርፕራይዞች ጊዜያዊ የገበያ ማዕከላትን በማቋቋም ምርት በስፋትና በዓይነት እንዲቀርብ ተደርጓል ብለዋል። በዚህም ከ94 ሺህ ሊትር በላይ ዘይት፣ 877 ኩንታል የዳቦ ዱቄት፣ ከ1 ሺህ 800 ኩንታል በላይ ስኳር፣ ሽንኩርትና ሌሎች ለበዓል ገበያ የሚያስፈልጉ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ መቻሉን ተናግረዋል። በተጨማሪም ከ18 ሚሊዮን ሊትር በላይ ወተት፣ ከ277 ሺህ በላይ ዶሮ፣ ከአንድ ሚሊዮን በላይ እንቁላል እንዲሁም ከ50 ሺህ በላይ የደለቡ በሬዎች፣ በጎችና ፍየሎች መቅረባቸውን አስረድተዋል። በዞኑ የአነደድ ወረዳ የአንበር ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ትግስት መላኩ እንደገለጹት፤ ገበያውን ለማረጋጋት የተደረገው ጥረት ህብረተሰቡ በአቅሙ ልክ የሚያስፈልገውን ገዝቶ ተደስቶ እንዲውል የሚያደርግ ነው። በዞኑ በማቻከል ወረዳ የአማኑኤል ከተማ ነዋሪ አቶ ይሁን አዲስ በበኩላቸው፤ ስኳርና እንቁላልን በመደበኛ ገበያ ካለው በቅናሽ ዋጋ እየገዙ መሆኑን ተናግረዋል። በተያያዘ ዜና ምዕራብ ጎንደር ዞን የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ ተወካይ አቶ መብራቱ አዲስ እንደገለጹት፤ በዓሉን አስመልክቶ የአቅርቦት እጥረትና ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር ከባለድርሻ አካላት ጋር እየተሰራ ነው። በተሰራው ስራም የእርድ እንስሳት፣ ዘይት፣ ስኳር፣ የዳቦ ዱቄትና ሌሎች መሰረታዊ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን በበቂ ሁኔታ ማቅረብ መቻሉን አረጋግጠዋል። በዞኑ ከ200 ሺህ በላይ ሰንጋ፣ ፍየልና በግ ለበዓሉ የቀረበ መሆኑን ጠቁመው ግብረ ሃይል በማቋቋም ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉና ምርት በሚደብቁ ህገወጦች ላይ ርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ጠቁመዋል። በገንዳውሃ ከተማ ሲገበያዩ ያገኘናቸው አቶ ገብረማርያም አዱኛ በሰጡት አስተያየት የእርድ እንስሳት እንቁላልና አንዳንድ ለበዓል የሚያስፈልጉ ምርቶች አቅርቦት ካለፉት ዓመታት የተሻለ ነው ብለዋል። ይህም ህብረተሰቡ በአቅሙ የሚፈልገውን ገዝቶ በዓሉን በደስታ ለማሳለፍ የሚያስችል ነው ብለዋል።
የነዳጅ አቅርቦት እጥረትን ለመቋቋም የተወሰደው የመፍትሄ አቅጣጫ ተግባራዊነቱ እንደቀጠለ ነው
Apr 9, 2026 93
ደሴ ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ የነዳጅ አቅርቦት እጥረትን ለመቋቋም የተወሰደው የመፍትሄ አቅጣጫ በተቀናጀ መልኩ ተግባራዊነቱ እንደቀጠለ መሆኑን የደሴ ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ አስታወቀ። በመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት ምክንያት የተከሰተውን የነዳጅ አቅርቦት ችግር ለመቋቋም በመንግስት በኩል ግብረ ሃይል ተቋቁሞ የተለያዩ የመፍትሄ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑ ይታወቃል። የነዳጅን አጠቃቀምን በቁጠባ ማድረግ፣ የታዳሽ ኃይል አማራጮችን የመጠቀም ልምድ፣ የእግር ጉዞ ባህልን ማጎልበት፣ የሕዝብ ትራንስፖርትን መጠቀም፣ በነዳጅ ግብይት ላይ የሚስተዋሉ ሕገ-ወጥ ተግባራትን መቆጣጠር ትኩረት የተደረገባቸው ጉዳዮች ሆነዋል። በደሴ ከተማ እና አካባቢው ያለውን የነዳጅ አጠቃቀምና አጠቃላይ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን አተገባበር በተመለከተ ኢዜአ የደሴ ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ዮናስ እንዳለ ጋር ቆይታ አድርጓል። ኃላፊውም በማብራሪያቸው የነዳጅ አቅርቦት እጥረትን ለመቋቋም የተወሰደው የመፍትሄ አቅጣጫ በተቀናጀ መልኩ ተግባራዊነቱ እንደቀጠለ መሆኑን ገልጸዋል። የእስካሁኑ ሂደት በብዙ መልኩ ሲታይ ውጤታማ እንደነበር አስታውሰው ችግሩ በዘላቂነት እስከሚፈታ ድረስ ለመፍትሄው በጋራ መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። የከተማ አስተዳደሩ ግብረ ሃይል በማቋቋም ቅድሚያ ለሚሰጠው በመስጠትና ሌሎች መንግስት ያስቀመጣቸውን አቅጣጫዎች ተግባራዊ ማድረግ መቻሉን አስታወሰው ይህም ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ተናግረዋል። ህብረተሰቡም ችግሩ አለም አቀፍ መሆኑን በመገንዘብ በእግሩ በመጓዝ፣ ጉዞዎችን በመቀነስ፣ በመተባበርና በመረዳዳት ያሳየው መልካም ተግባር የከፋ ችግር እንዳይፈጠር አስችሏል ብለዋል። በደሴ ከተማ የህዝብ ትራንስፖርት አሽከርካሪ የሆነው ወጣት ሰይድ ይመር፤ የምናገኘውን ነዳጅ በአግባቡ በመጠቀም የህዝብ አገልግሎት እየሰጠን እንገኛለን፤ አጠናክረንም እንቀጥላለን ብሏል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ታደሰ ኪዳነማሪያም፤ የነዳጅ አቅርቦት ችግሩ ፈታኝ ቢሆንም ለቀጣይ ብዙ የሚያስተምረን ነገር አለ ብለዋል። የነዳጅ አቅርቦት ችግሩን ተቋቁሞ ለማለፍ በመንግስት የተቀመጡ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን አድንቀዋል። በተለይም የነዳጅ ጥገኝነትን በመቀነስ አማራጭ መንገዶችን ማብዛትና የኤሌክትሪክ ሃይል ልማትን ማስፋት ተገቢ መሆኑን አንስተዋል።
በጅግጅጋ ከተማ ለበዓል ገበያ የእርድ እንስሳትና የፍጆታ ምርት በበቂ ሁኔታ ቀርቧል
Apr 9, 2026 78
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦በጅግጅጋ ከተማ ለበዓል ገበያ በቂ የእርድ እንስሳትና የግብርና ምርቶች አቅርቦት መኖሩን ሸማቾችና ነጋዴዎች ገለጹ። በጅግጅጋ ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው ነጋዴዎችና ሸማቾች ለዘንድሮው የትንሣዔ በዓል በከተማዋ በቂ የእርድ እንስሳትና ሌሎች የፍጆታ ምርቶች አቅርቦትና ግብይት መኖሩን ገልጸዋል። ወይዘሮ ሲሃም በድሪ በአትክልት ምርቶች ንግድ ላይ የተሠማሩ ሲሆኑ በበዓል ገበያው በቂ ምርት መኖሩን በመግለፅ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል።   በምርቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ አለመታየቱን እና በአሁን ወቅት በምርት አቅርቦት በኩል ችግር አለመኖሩን ገልጸዋል። ከፍየል ነጋዴዎች መካከል ወይዘሮ አሚና ዩሱፍ በገበያው በቂ የእርድ እንስሳት መቅረቡን ተናግረዋል። በእንቁላል ምርት ሽያጭ ላይ የተሠማሩት አቶ ታረቀኝ ጀምበሩ በበኩላቸው ለበዓሉ በቂ ምርት መኖሩን ጠቅሰዋል። የጅግጅጋ ከተማ ንግድና ገበያ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ወይዘሮ ለይላ መሀመድ በበኩላቸው፤ ለትንሳኤ የበዓል ገበያ የግብርናና የፋብሪካ ምርቶች እጥረት እንዳይፈጠር ከህብረት ስራ ማህበራት ጋር በቅንጅት መሰራቱን አንስተዋል። የበዓል ምርቶቹን በበቂ ሁኔታ ከማቅረብ ባለፈ ህገ ወጥ ንግድን ለመቆጣጠር ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
በድሬዳዋ መንግስት በነዳጅ አጠቃቀምና ስርጭት ላይ ያስቀመጠው መመሪያ በአግባቡ እየተተገበረ ነው
Apr 9, 2026 70
ድሬዳዋ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦) መንግስት በነዳጅ አጠቃቀምና ስርጭት ላይ ያስቀመጣቸው መመሪያዎችና አቅጣጫዎች በአግባቡ በመተግበር ላይ መሆናቸውን የድሬዳዋ አስተዳደር ንግድ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አሚኖ ጣሃ ተናገሩ። የመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በዓለም አቀፍ ደረጃ በነዳጅ አቅርቦትና ግብይት ላይ መጠነ ሰፊ ችግሮችና ተፅዕኖዎችን አስከትሏል። ኢትዮጵያም ሊደርስ የሚችለውን ተፅዕኖ ለመቋቋም የሚያስችሉ የተለያዩ የመፍትሄ አቅጣጫዎች እና መመሪያዎችን ዘርግታ ተግባራዊ እያደረገች ትገኛለች። በድሬዳዋ በነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ላይ ሊገጥም የሚችለውን ችግር ለመቋቋም የተቀመጡ የመፍትሄ አቅጣጫዎች በአግባቡ በመተግበር ላይ መሆኑን የአስተዳደሩ ንግድ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አሚኖ ጣሃ ለኢዜአ ተናግረዋል። የአስተዳደሩ የፍትህና ፀጥታ ተቋማትና ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት የተካተቱበት ግብረ ኃይል ተቋቁሞ መመሪያው በአግባቡ እንዲተገበር በትኩረት እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በከተማው በሚገኙ 30 የነዳጅ ማደያዎች ለሊት ጭምር ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ ነዳጅን በተቀመጠው መመሪያ በፍትሃዊነት ተደራሽ እያደረጉ መሆኑንም አንስተዋል። በየማደያዎቹም ከጅቡቲ ነዳጅ ለሚያጓጉዙት፣ ወደ ውጭ የሚወጡ ምርቶችን ለሚያመርቱት የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪዎችና ሌሎችም ቅድሚያ በመስጠት እንቅስቃሴያቸውን በማሳለጥ ላይ መሆናቸውን በመግለፅ። የተቀሩትም መንግስት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት የስርጭቱ ተጠቃሚ እየሆኑ ናቸው ብለዋል። የመንግስት ተሸከርካሪዎችም ነዳጅን በቁጠባና በጋራ እንዲጠቀሙ እየተደረገ መሆኑንም አንስተዋል። የብዙሃን ትራንስፖርትና ሀገር አቋራጭ ተሸከርካሪዎች እንዲሁም ትኩረት ለሚሹ አገልግሎት ሰጪ የአስተዳደሩ ተቋማትም ነዳጅ እንዲደርሳቸው እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን መንግስት ያወጣውን መመሪያ ያላከበሩ አራት ማደያዎች የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ በመስጠት ከድርጊታቸው እንዲመለሱ መደረጉንም አቶ አሚኖ አውስተዋል። በአንጻሩ መመሪያዎችን በግንባር ቀደምትነት ተቀብለው በተሳካ መንገድ እየፈፀሙ የሚገኙ 8 ማደያዎች ደግሞ አስተዳደሩ ምስጋናና ዕውቅና እንደሰጣቸው በማስታወስ። ኢዜአ ያነጋገራቸው አሽከርካሪዎች በበኩላቸው መንግስት በከፍተኛ ድጎማና ውስብስብ ችግር የሚያቀርበውን ነዳጅ በቁጠባና ከብክነት በፀዳ መንገድ ማሰራጨቱ ወቅታዊ ችግር የሚያሻግር መሆኑን ገልጸዋል። አቶ ወንድወሰን አበራ እና ሸምሰዲን ኢድሪስ የተባሉ የህዝብ ትራንስፖርት አሽከርካሪዎች በበኩላቸው እንዳሉት፤ መመሪያው ነዳጅን በፍትሃዊነት ለማሰራጨትና ለመቆጠብ የሚያስችል መፍትሄ ነው ብለዋል።
ከለውጡ ወዲህ ለቱሪዝም ተኮር የቅርስ ልማት የተሰጠው ትኩረት የኢትዮጵያን ቱሪዝም ወደ አዲስ ምዕራፍ እያሸጋገረ ነው
Apr 9, 2026 150
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦መንግሥት ለቱሪዝም ተኮር የቅርስ ጥበቃና ልማት የሰጠው ልዩ ትኩረት ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን በማድረግ ለዘርፉ ዕድገት የጎላ ሚና እየተጫወተ መሆኑን የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን አስታወቀ። ባለፉት የለውጥ ዓመታት መንግሥት ለቱሪዝም ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረትና በነደፈው የብዝኃ ዘርፍ ፖሊሲ አማካኝነት፣ ለዘመናት የተዘነጉ በርካታ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ ቅርሶች ተገቢውን ጥገናና እድሳት አግኝተው ለጎብኚዎች ክፍት ሆነዋል።   የጎንደር አብያተ መንግሥታት፣ ብሔራዊ ቤተ መንግሥት፣ ጂማ አባ ጅፋር ቤተ መንግሥት፣ ሐረር ጀጎል ግንብ፣ ሶፍ ኡመር ዋሻን ጨምሮ በአዲስ አበባና ሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚገኙ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ ቅርሶች ደረጃቸውን በጠበቀ መልኩ ታድሰው ለጎብኝዎች ክፍት ሆነዋል። የኢትዮጵያ የቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር አበባው አያሌው ለኢዜአ እንደገለጹት፣ መንግሥት ዘርፉን ለማሳደግ በወሰደው ቁርጠኝነት ቋሚና ተንቀሳቃሽ ቅርሶችን የማልማት ተግባር በውጤታማነት እየተከናወነ ይገኛል። በተለይም ለባህልና የከተማ ቱሪዝም ትኩረት በመሰጠቱ ተጨባጭ ለውጦች መመዝገቡን በማንሳት፥ የኢትዮጵያ የቅርስ ልማት ሥራ የቱሪዝም ዘርፉን ወደ አዲስ ምዕራፍ እያሸጋገረ ነው ብለዋል። በለውጡ ዓመታት የዓድዋ ድል መታሰቢያን ጨምሮ የኢትዮጵያን ክብርና ታሪክ ከቱሪዝም የሚያስተሳስሩ ሙዚየሞችም መገንባታቸውን ገልጸዋል። የቅርስ ቦታዎችን የማዘመን ስራ የኢትዮጵያን ገጽታ ከመገንባቱ ባለፈ፣ የጎብኝዎችን ቁጥር በመጨመር የቱሪዝም ገቢን ማሳደጉንና ለዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል መፍጠሩን አንስተዋል። ቅርሶች በዩኔስኮ እንዲመዘገቡ የተደረገው ጥረት ለሀገሪቱ ታሪካዊ እሴቶች ተገቢውን ክብር አስገኝቷል ብለዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት 19 ቅርሶችን በዩኔስኮ በማስመዝገብ በአፍሪካ ቀዳሚ ሥፍራ መያዟን ረዳት ፕሮፌሰር አበባው ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅትም ቋሚና የማይዳሰሱ ቅርሶችን የማስመዝገብ ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን አስታውቀዋል።   ከማይዳሰሱ ቅርሶች መካከልም የአገው ፈረስ ባህል፣ የሀላባ የዘመን መለወጫ 'ሴራ' እንዲሁም ዋዛ የሙዚቃ መሳሪያ ጨዋታ (ዙምባራ) በዩኔስኮ እንዲመዘገቡ ቀርበዋል ነው ያሉት። የመጥፋት አደጋ የተጋረጠባቸውና አስቸኳይ ጥበቃ የሚያስፈልጋቸውን ቅርሶች ለመጀመሪያ ጊዜ ለማስመዝገብ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በጣና ሐይቅ የሚገኙ ደሴቶችንና የአልነጃሺ ታሪካዊ መንደርን በዩኔስኮ ለማስመዝገብ የተጀመሩ ሥራዎች በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። ቀደም ሲል በዩኔስኮ የሚመዘገቡ ቅርሶች ትኩረት ያደረገው የባህል ቅርሶች ላይ መሆኑን አንስተው በአሁኑ ወቅትም የተፈጥሮ ቅርሶችን ለማስመዝገብ እየተሰራ ነው ብለዋል።
ጅቡቲ ለኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ጭነቶች ቅድሚያ የመስጠት ተግባሯን ትቀጥላለች
Apr 9, 2026 114
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ ጅቡቲ ወደ ኢትዮጵያ ለሚጓጓዙ ጭነቶች ቅድሚያ መስጠቷን አጠናክራ እንደምትቀጥል የጅቡቲ ወደቦችና ነፃ የንግድ ቀጣና ባለስልጣን (DPFZA) ሰብሳቢ አቡበከር ዑመር ሃዲ ገለጹ። የጅቡቲ ወደቦችና ነፃ የንግድ ቀጣና ባለስልጣን (DPFZA) ሰብሳቢ አቡበከር ዑመር ሃዲ የጅቡቲ ባህር ወደቦች በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ የመጣውን የጭነት መጠን ያለምንም መጨናነቅ ማስተናገድ የሚችል አስተማማኝ አቅም እንዳላቸው ለኢዜአ ገልጸዋል። ወደ ወደብ የሚመጡ ማናቸውም የኢትዮጵያ ጭነቶች በተለይም ማዳበሪያ ሳይዘገዩ ወደ መሐል ሀገር እንዲጓጓዙ ቅድሚያ እየተሰጣቸው መሆኑን ተናግረዋል። ላለፉት በርካታ ዓመታት ጅቡቲ ከ90 በመቶ በላይ የሚሆነውን የኢትዮጵያን የገቢና ወጪ ንግድ እያስተናገደች ትገኛለች። ይህ ታሪካዊ ትስስር የሁለቱ ሀገራት ወንድማማችነት ይበልጥ እንዲጠናከር ምክንያት ሆኗል። የሁለቱን ሀገራት የንግድ ትስስር በማቀላጠፍ ረገድ ዘመናዊውና በኤሌክትሪክ የሚሰራው የአዲስ አበባ-ጅቡቲ የምድር ባቡር ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ይህ ስትራቴጂካዊ የትራንስፖርት ኮሪደር የሎጂስቲክስ ቅልጥፍናን በማሻሻል የትራንዚት ጊዜን በእጅጉ መቀነስ ያስቻለ ሲሆን፣ የንግድ እንቅስቃሴውን ፈጣንና ውጤታማ አድርጎታል። በኢትዮጵያ እየታየ ያለው የኢንዱስትሪ መስፋፋት፣ የመሠረተ ልማት ግንባታና የንግድ ዕድገት ለወደብ አገልግሎት ፍላጎት ማደግ ምክንያት ሆኗል። በወደብ ስራዎች ላይ አልፎ አልፎ የሚታዩ የመርከቦች የአንድ ወይም የሁለት ቀናት መዘግየቶች ከዓለም አቀፍ አሰራር አንጻር የተለመዱ መሆናቸውንም አንስተዋል። ሀገራቱ ያላቸውን ጠንካራ የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ ለማገዝ፣ ጅቡቲ በአንዳንድ የወደብ ሀብቶች ላይ ኢትዮጵያ የባለቤትነት ድርሻ (አክሲዮን) እንዲኖራት ሃሳብ ማቅረቧን ጠቁመዋል። ይህ አዲስ አቀራረብ የሁለቱን ሀገራት ኢኮኖሚያዊ ትስስር ወደ ላቀ የባለቤትነት ደረጃ የሚያሸጋግርና ለዘላቂ ጥቅማቸው ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል። በየብስ ትራንስፖርት በተለይም በባቡርና በመኪና መንገድ ላይ የሚታዩ ጫናዎችን ለማቃለል ጅቡቲ አዳዲስ ስልቶችን እየቀረጸች መሆኑም ታውቋል። ከመርከብ ወደ መርከብ የሚደረጉ የጭነት ማስተላለፍ (Transshipment) ስራዎችን በማስፋፋትና ተጨማሪ የማከማቻ መጋዘኖችን በመገንባት የሎጂስቲክስ ዘርፉን ይበልጥ ዘመናዊ ለማድረግ ታቅዷል።
በአማራ ክልል በከተማ ክላስተር ዘርፍ አመርቂ ስኬቶች ማስመዝገብ ተችሏል
Apr 8, 2026 305
ባህር ዳር፤ መጋቢት 30/2018(ኢዜአ) ፦በአማራ ክልል በከተማ ክላስተር ዘርፍ አመርቂ ስኬቶችን ማስመዝገብ መቻሉን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሃመድ (ዶ/ር) ገለፁ። ‎በክላስተሩ ተቋማት በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት የተከናወኑ ተግባራትን የሚገመግም የውይይት መድረክ ዛሬ በባህር ዳር ከተማ ተካሂዷል።   ‎በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሃመድ (ዶ/ር) በመድረኩ እንደገለጹት፤ አመራሩ ከባለሙያው ጋር ባደረገው ቅንጅት በከተማ ክላስተር ዘርፍ ስኬት ሊመዘገብ ችሏል። ‎ለዚህም ‎በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን፣ በሆቴልና ቱሪዝም፣ የኢንዱስትሪ መንደሮችን በማስፋፋት፣ በሥራ ዕድል ፈጠራና ገጠርን ከከተማ በማስተሳሰር የተገኘ ውጤት መሆኑን አስረድተዋል። ‎ሥራውም ‎በተለይ የኮሪደር ልማት የከተሞችን ውበትን የገለጠ፣ የህብረተሰቡን የሥራ ባህል የቀየረ እና ከተሞችን ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ተመራጭ ያደረገ ነው ብለዋል። ‎‎እንደ አህመዲን (ዶ/ር) ገለጻ ለውጭ ባለሃብቶች ብቻ ተፈቅዶ የነበረው በኢንዱስትሪ መንደሮች ገብቶ የማልማት ሥራ ለሀገር ውስጥ ባለሃብቶችም መፈቀዱ የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ዘርፉ እንዲነቃቃ አድርጓል። ‎‎‌በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን በኩልም 5 ሚሊዮን ዜጎች የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ማውጣታቸውን ጠቅሰው በኢትዮ-ኮደርስ በርካታ ወጣቶችና ሠራተኞች የስልጠናው ተጠቃሚ ሆነዋል ብለዋል። ‎‎በቀሪ ወራትም በከተማ ክላስተር ዘርፍ የተመዘገቡ ስኬቶችን በማስቀጠልና ክፍተቶችን በማረም የላቀ አፈጻጸም ለማስመዝገብ እንደሚሰራ አመልክተዋል።   ‎‎የክልሉ ከተሞችና መሰረተ ልማት ቢሮ አማካሪ አቶ ሽቤ ክንዴ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ በ32 ከተሞች የእግረኛና የብስክሌት መንገዶች፣ የአረንጓዴ ልማትና የመዝናኛ ስፍራዎችን ያሟላ የኮሪደር ልማት ግንባታ እየተከናወነ ነው። ‎በቀሪው ጊዜም በዕቅድ የተያዘውን በጥራት ገንብቶ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ለማብቃት ጥረት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፣ ህብረተሰቡም በልማቱ ንቁ ተሳትፎ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። የአማራ ከልል ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ የቻለ ይግዛው፤ የክላስተር ቢሮዎች አሰራራቸውን እንዲያዘምኑና የሚሰጡት አገልግሎት ቀልጣፋና ተደራሽ እንዲሆን ለማድረግ ቢሮው በትኩረት እየሰራ መሆኑን አንስተዋል።   በኢንቨስትመንት፣ በንግድና ገበያ ልማት፣ በቱሪዝምና ሌሎች ተቋማት የዲጂታል ቴክኖሎጂ አሰራርን በማስፈን ለህብረተሰቡ የሚሰጡ አገልግሎቶች ቀልጣፋ፣ ፍትሃዊና ከብልሹ አሰራር የጸዱ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። ‎የዲጂታል ትግበራውም የክልሉን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መስተጋብር ከማፋጠን ባሻገር ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድግ አበረታች ውጤት እያስገኘ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ‎‎‎‎‎በውይይት መድረኩ ላይ በክላስተሩ ሥር የሚገኙ ተቋማት ሃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት በመሳተፍ ላይ ናቸው።
በገንዳውኃ ከተማ በህገ ወጥ መንገድ የተከማቸ ከ950 ሊትር በላይ ነዳጅ ተያዘ
Apr 8, 2026 289
ገንዳውኃ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን ገንዳውኃ ከተማ በህገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የነበረ ከ950 ሊትር በላይ ነዳጅ መያዙን የከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኢንስፔክተር ሀይሌ ብርሃኑ 900 ሊትር ናፍጣ እና 56 ሊትር ቤንዚን በግለሰብ ቤት ከተደበቀበት ለመያዝ መቻሉን ገልጸዋል።   በህገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የነበረው ነዳጅ ሊያዝ የቻለው የጸጥታ አካላት ባደረጉት ድንገተኛ ፍተሻና ጥብቅ ክትትል መሆኑንም ተናግረዋል። እንደ ኃላፊው ገለጻ ነዳጁ በህገወጥ መንገድ ተከማችቶ የተገኘው በከተማው ቀበሌ 03 ልዩ ቦታው ቀጠና 08 በተባለ አካባቢ ነው።   በቀጣይም በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ጫና የሚፈጥሩ መሰል ህገ ወጥ ተግባራትን ለመከላከል የቁጥጥር ሥራው ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ህብረተሰቡ ህገ ወጥ ተግባር ተፈጽሞ ሲያይ ለጸጥታ አካላት ፈጥኖ ጥቆማ በመስጠት እያደረገ ያለውን ትብብር በቀጣይም አጠናክሮ እንዲቀጥል ኃላፊው ጥሪ አቅርበዋል።
የጉምሩክ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ የጉምሩክ አገልግሎት በሚያቀላጥፍ መልኩ እየተዘጋጀ ነው
Apr 8, 2026 165
አዲስ አበባ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦የጉምሩክ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ የጉምሩክ አገልግሎት በሚያቀላጥፍ መልኩ እየተዘጋጀ መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። ቋሚ ኮሚቴው በጉምሩክ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። በዚሁ ወቅት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ደሳለኝ ወዳጆ፤ በረቂቅ አዋጁ ሥርዓት ክፍተትን የሚያርሙ ድንጋጌዎች እንደተካተቱ ገልጸዋል።   የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፍ የንግድ ተወዳዳሪነትን የሚያሳልጥ ዓለም አቀፍና አዳዲስ የጉምሩክ አገልግሎት ማቀላጠፊያ ድንጋጌዎች መካተታቸውን ተናግረዋል። በዚህም የአዋጁ ማሻሻያ የኮሚሽኑን ተግባርና ኃላፊነት በተቀላጠፈ የአሰራር ሥርዓት በመምራት ውስብስብ የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴን መግታት በሚያስችል መልኩ እየተዘጋጀ ነው ብለዋል። የምክር ቤቱ አባላትና የሕግ ሙያተኞችም፤ በረቂቅ አዋጅ ላይ ምላሽና ማብራሪያ የሚሹ ጉዳዮችን በማስመልከት ለሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች አስተያየትና ጥያቄ አቅርበዋል። በረቀቂ አዋጁ ላይ የገቢ ምርቶችን የቆይታ ጊዜ በማስመልከት ከዚህ ቀደም ከነበረው አንፃር ሲታይ ከፍ እንዲል መደረጉን በማስመልከት ምላሽና ማብራሪያ ጠይቀዋል።   የጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ በምላሽና ማብራሪያቸው፤ የጉምሩክ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ከዚህ ቀደም የነበሩ የአሰራር ክፍተቶችን ለማረም ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። በዚህም በረቂቅ አዋጁ ውስብስብ የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴን መከላከል የሚያስችሉ ወሳኝ ድንጋጌዎችን በማካተት እየተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል። የጉምሩክ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አዘዘው ጫኔ በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያን የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት የሚያቀላጥፍ አስቻይ የጉምሩክ አገልግሎት አሰጣጥ ተቋማዊ የሪፎርም አካል መሆኑን ገልጸዋል።   በተጨማሪም በዕቃዎች የጉምሩክ ሥነ-ሥርዓት የሚጠናቀቅበት ጊዜ፣ የዋጋ አወሳሰን፣ በይግባኝ አቀራረብ፣ በጉምሩክ ጥሰት የሚወረሱ ንብረቶች አስተዳደር፣ የዋስትና አያያዝ ላይ የተደረጉ ጉልህ ማሻሻያዎች ላይም ማብራርያ ሰጥተዋል። በገንዘብ ሚኒስቴር የታክስ ጉዳዮች አማካሪ ዋሲሁን አባተ፤ በረቀቂ አዋጁ ላይ የጉምሩክ ሥነ-ስርዓትን ያሟላ አገልግሎት መስጠት የሚያስችሉ ወሳኝ ድንጋጌዎች መካተታቸውን አስረድተዋል። በዚህም በረቂቅ አዋጁ ላይ የጉምሩክ አገልግሎቶችን የሚያቀላጥፉ አመቺና አዳዲስ ዓለም አቀፍ የአሰራር ሥርዓት መርሆችና ድንጋጌዎች እንደተካተቱ አስገንዝበዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም