ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭትን በማሳለጥ በኩል ከፍተኛ ለውጥ አስገኝቷል
May 23, 2026 120
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭትን በማሳለጥ በኩል ከፍተኛ ለውጥ ማስገኘቱን ኢዜአ ያነጋገራቸው አሽከርካሪዎች እና የነዳጅ ማደያዎች ገለጹ፡፡ በመካከለኛው ምስራቅ ተከስቶ የነበረውን ችግር ተከትሎ በዓለም አቀፍ ደረጃ በነዳጅ ምርት አቅርቦት ላይ የተፈጠረው ክፍተት፣ በሀገር ውስጥም የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል አስከትሎ የነበረ ቢሆንም፤ መንግሥት አቅርቦቱ ከጦርነቱ በፊት ወደነበረበት ደረጃ እንዲመለስ አድርጓል። መንግሥት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ የነበረውን ዓለም አቀፍ ተጽዕኖ ተቋቁሞ ለማለፍ ያስቻለ ሲሆን፣ አሁን ላይ በተለያዩ ከተሞች የተረጋጋ፣ ቀልጣፋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት እንዲኖር አስችሏል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ሚያዝያ 21 ቀን 2018 ዓ.ም በወቅታዊ የዓለም የነዳጅ ሁኔታን በማስመልከት በሰጡት ማብራሪያ፣ የናፍጣ ነዳጅ አቅርቦት ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት ወደነበረበት እንዲመለስ መደረጉን መጥቀሳቸው ይታወቃል፡፡ ኢዜአ በመዲናዋ ያነጋገራቸው አሽከርካሪዎችና የነዳጅ ማደያ ባለቤቶች፤ መንግሥት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደውን የማሻሻያ እርምጃ ተከትሎ በአቅርቦቱና በስርጭቱ ላይ ከፍተኛ አዎንታዊ ለውጥ መታየቱን ገልጸዋል።   አስተያየት ከሰጡ አሽከርካሪዎች መካከል አባይነህ ይሁኔ፤ ቀደም ሲል ከዓለም አቀፉ የነዳጅ እጥረት ጋር ተያይዞ በነበረው መስተጓጎል በእለት ተእለት እንቅስቃሴያቸው ላይ ከፍተኛ ችግር ገጥሟቸው እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ላይ ግን የነበረው ችግር ሙሉ በሙሉ ተፈትቶ ሁኔታው ወደ ቀድሞው በመመለሱ፣ በሁሉም ማደያዎች የሚፈልጉትን ያህል ነዳጅ ያለምንም እንግልት እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡   ሌላኛው አሽከርካሪ ከድር ሁሴን በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል ነዳጅ ለማግኘት እስከ አንድ ሳምንት ይወስድባቸው የነበረው አስቸጋሪ ሁኔታ በአሁኑ ወቅት ሙሉ በሙሉ መፈታቱንና ያለምንም እንግልት ነዳጅ እያገኙ ማኅበረሰቡን በሚገባ እያገለገሉ መሆናቸውን አስረድተዋል።   በተመሳሳይ አሽከርካሪ ተፈሪ ዓለሙ እና ረታ ጂቢቲ እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል ተከስቶ የነበረው የነዳጅ እጥረትና የረጅም ሰዓት ወረፋ በመንግሥት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት በመቀረፉ፣ በአሁኑ ወቅት ያለምንም መስተጓጎል እየተስተናገዱ ይገኛሉ።   በነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ላይ የነበረው ችግር በመወገዱ በአሁኑ ወቅት የተረጋጋ ሁኔታ መፈጠሩንና መደበኛ ሥራቸውን በተሻለና ይበልጥ ውጤታማ በሆነ መልኩ እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። የነዳጅ ማደያ ሱፐርቫይዘሮች በበኩላቸው ቀደም ሲል በዓለም አቀፍ የነዳጅ ቀውስ ምክንያት ይፈጠር የነበረው የአቅርቦት ችግር በመቀረፉ ደንበኞቻቸውን ያለምንም እንግልት እያስተናገዱ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በአቅርቦትና በስርጭት ላይ ችግር አለመኖሩን ጠቁመው ለማኅበረሰቡ ጥሩ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በቡልጋሪያ አካባቢ የቶታል ማደያ ሱፐርቫይዘር ሰለሞን ገብረሕይወት እና በአሮጌው ቄራ አካባቢ ቶታል ማደያ ሱፐርቫይዘር ይርጋ ኪዳነ ማርያም ቀደም ሲል በነበረው እጥረት ምክንያት ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ለማግኘት እስከ አምስት ቀናት የሚደርስ ረጅም ሰልፍ ይጠብቁ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ላይ ችግሩ ሙሉ በሙሉ መቀረፉን አረጋግጠዋል።   በተመሳሳይ የሜክሲኮ አካባቢ የካምፖ አስመራ ነዳጅ ማደያ ሱፐርቫይዘር ጥበቡ በቀለ በበኩላቸው፤ መንግሥት ዓለም አቀፉን የነዳጅ አቅርቦት ቀውስ ለማስተካከል የወሰደውን ቁርጠኛ እርምጃና የመጣውን ፈጣን አዎንታዊ ለውጥ አድንቀዋል። በአሁኑ ወቅት ነዳጅ ለማደያቸው በአግባቡና በወቅቱ እየቀረበ መሆኑን ገልጸው እያገኙት ያለውን ምርትም ለተጠቃሚ አሽከርካሪዎች እያቀረቡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።
የአካባቢ ጸጋዎችን መሰረት ያደረጉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ ነው
May 23, 2026 100
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በየአካባቢው የሚገኙ የፈጠራና የተፈጥሮ ጸጋዎችን በመለየትና የሥራ ዕድሎችን በማስፋፋት ተጨባጭ ውጤቶች እየተገኙ መሆኑን የተለያዩ ክልሎች የሥራና ክህሎት ቢሮ የሥራ ኃላፊዎች ገለጹ። በኢትዮጵያ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ፣ የግል ዘርፉን ለማበረታታትና የሥራ አጥነት ቁጥርን ለመቀነስ በርካታ መዋቅራዊና ሕጋዊ ሪፎርሞች ተከናውነዋል። ለአብነትም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ማስፋፋት፣ ለሥራ ዕድል ቅድሚያ የሚሰጥ ስትራቴጂ ትግበራ፣ ተቋማዊ ሪፎርም እንዲሁም የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪትን ማመቻቸት በዋናነት የሚጠቀሱ ተግባራት ናቸው።   የተለያዩ ክልሎች የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአካባቢ ጸጋዎችን በጥናት በመለየት የሥራ ዕድልን ለማስፋፋት የተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶችን አስገኝተዋል። የአካባቢውን ጸጋ ተጠቅመው ዜጎች በማኅበረሰብና በቤተሰብ የንግድ ሥራዎች ላይ እንዲሰማሩ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን አመልክተው፤ የሥልጠና፣ የብድር እና የሌሎች ተያያዥ ድጋፎችን በማድረግ የዜጎች ውጤታማነት ይበልጥ እየጎለበተ መምጣቱን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት አማካኝነት የሥራ ፈላጊዎች ምዝገባና የሥራ ዕድል ፈጠራ መረጃዎችን በዘመናዊ መልኩ በማደራጀት፣ ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተደራሽ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ኃላፊዎቹ ጠቁመዋል።   የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ ተመስገን ኃይሌ፤ በክልሉ የሀገር ውስጥ የሥራ ዕድሎችን ለማሳደግ የአካባቢ ጸጋዎችን በመለየት ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ለዜጎች የክህሎት፣ የአቅም ግንባታና ሌሎች ድጋፎችን በማመቻቸት እና የሥራ ዕድል ፈጠራው ክህሎት መር በማድረግ እስካሁን ለ280 ሺህ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቁመዋል፡፡   በሲዳማ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ከፍያለው ከበደ በበኩላቸው፤ በክልሉ በስፋት የሚገኙ ምርቶችን በመለየት የማኅበረሰብና የቤተሰብ የንግድ ሥራዎችን ከሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ጋር በማስተሳሰር ውጤታማ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ የሥራ ስምሪትና ገበያ ልማት ዘርፍ ኃላፊ ዘውዱ ሳሙኤል፤ በክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት ያደረገው በአካባቢ ጸጋዎችና አቅሞች ላይ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ዜጎች ተደራጅተው በአካባቢው በሚገኙ ጸጋዎች ላይ እሴት በመጨመር በስፋት እንዲያመርቱና ወደ ገበያ እንዲያስገቡ በማድረግ በኩል ስኬታማ ሥራዎች መከናወናቸውን አስገንዝበዋል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን በመጪው ክረምት በ39 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ ይተከላል
May 23, 2026 97
ነቀምቴ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን በመጪው ክረምት በ39 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ እንደሚተከል የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በጽህፈት ቤቱ የቡና ምርት ቡድን መሪ አሰፋ መኮንን እንደገለጹት፤ በዞኑ የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተተገበረ ባለው ኢኒሼቲቭ የአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት እያደገ መጥቷል። በተያዘው ዓመት ክረምትም በ39 ሺህ 983 ሄክታር መሬት ላይ በአጭር ጊዜ ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ 279 ሺህ 632 የቡና ችግኝ ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ብለዋል። ችግኞቹም በመንግስት፣ በማህበራትና በአርሶ አደሮች የችግኝ ጣቢያዎች እንዲባዙ ተደርጎ በአሁኑ ወቅት ለተከላ ዝግጁ መደረጉን ገልጸዋል።   ከችግኝ ዝግጅትና ተከላ ጋር ተያይዘው የሚታዩ ክፍተቶችን ለማረምም የባለሙያዎች የአቅም ግንባታና የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ እየተሰጠ ነው። የቡና ምርትና ምርታማነትን በተሻለ ደረጃ ለማሳደግ ያረጀና ምርት የማይሰጥ የቡና ተክል ጉንደላ ሲከናወን መቆየቱን ጠቅሰው የተጎነደሉ ተክሎች በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ መልሰው ምርት የሚሰጡ መሆኑንም ተናግረዋል። በዞኑ የጉቶ ጊዳ ወረዳ አርሶ አደር ሹምዬ ባይሳ እና አርሶ አደር ገመቹ ደረጄ በሰጡት አስተያየት፤ ቀደም ሲል በባህላዊ መንገድ ያመርቱ ስለነበር በሚፈለገው ልክ መጠቀም እንዳልቻሉ ገልጸዋል።
በአማራ ክልል የከተማ ነዋሪዎችን የቤት ባለቤት ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
May 23, 2026 85
ጎንደር፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የከተማ ነዋሪዎችን የቤት ባለቤት ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) ገለጹ። የጎንደር ከተማ አስተዳደር በ550 የመኖሪያ ቤት ሕብረት ሥራ ማኅበራት ለተደራጁ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች የቤት መስሪያ ቦታ፣ የሳይትና የብሎክ ርክክብ መርሃ ግብር አካሂዷል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የቢሮው ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ የክልሉ መንግሥት የቤት ልማት ፖሊሲና ስትራቴጂውን ወደ ተግባር በማውረድ፣ በመካከለኛና በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የኅብረተሰብ ክፍሎችን በተለያዩ አመራጮች የቤት ባለቤት ለማድረግ እየሠራ ነው። መንግሥት የሕዝቡን አቅም በማስተባበርና ዘመናዊ አሠራር በመዘርጋት የቤት አቅርቦት ችግርን ለመፍታት የተቀናጀ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። መሬት ውድና ውስን ሀብት በመሆኑ ለጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ትኩረት በመስጠት፣ ለኑሮ ምቹና ውብ የሆኑ ዘመናዊ ከተሞችን ለማስፋፋት የቤት ልማት ፖሊሲውን መሠረት ያደረጉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። የጎንደር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው በበኩላቸው፤ በማኅበራት የተደራጁ ነዋሪዎች ፈጥነው ወደ ግንባታ መግባት እንዲችሉ ከተማ አስተዳደሩ መሠረተ ልማቶችን በፍጥነት እንደሚያሟላ ገልጸዋል። ማኅበራቱ በገቡት ውል መሠረት ግንባታቸውን በፍጥነት መጀመር እንዳለባቸው ያሳሰቡት ምክትል ከንቲባው፤ መሬት አጥረው ለረጅም ዓመታት በሚያቆዩ ማኅበራት ላይ ጥብቅ ክትትል በማድረግ ከተማ አስተዳደሩ ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቀዋል። የከተማ አስተዳደሩ የመሬት መምሪያ ኃላፊ አቶ ታዛዙ በጽሐ፤ በዛሬው ዕለት የቅየሳና የብሎክ ሥራ ተሠርቶላቸው የመኖሪያ ቤት ግንባታ ቦታ ተጠቃሚ የሆኑት ከ13 ሺህ በላይ አባላትን ያቀፉ 550 የቤት ሥራ ማኅበራት መሆናቸውን አስታውቀዋል። ለእያንዳንዱ የማኅበር አባል 150 ካሬ ሜትር የግንባታ ቦታ መዘጋጀቱን የጠቆሙት ኃላፊው፤ ከተጠቃሚዎቹ መካከል የመንግሥት ሠራተኞች፣ መምህራንና የጤና ባለሙያዎች፣ ሴቶች፣ ወጣቶችና አካል ጉዳተኞች፣ በክብር የተመለሱ የሠራዊት አባላት፣ እንዲሁም ከስደት ተመላሾች እንደሚገኙበት አስረድተዋል። የቤት መስሪያ ቦታ ተጠቃሚ ከሆኑት ነዋሪዎች መካከል አቶ ታደለ በላይ በሰጠው አስተያየት፤ ለረጅም ዓመታት በግለሰብ ቤት ኪራይ አስቸጋሪ ሕይወት ሲመራ መቆየቱን ገልጾ፣ አሁን ቦታውን በማግኘቱ ፈጥኖ በመገንባት የቤት ባለቤት ለመሆን መወሰናቸውን ተናግረዋል። ወጣት አማኑኤል ምሕረቱ በበኩሉ፤ የቤት መስሪያ ቦታ ዕድለኛ በመሆኑ የተሰማውን ከፍተኛ ደስታ ገልጿል። በዚሁ የርክክብ ሥነ-ሥርዓት ላይ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በቤት ሥራ ማኅበራት የተደራጁ በርካታ የከተማዋ ነዋሪዎች ተገኝተዋል።  
የግራንዴር ሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ የሚያደርግ ነው
May 23, 2026 175
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የግራንዴር ሴራሚክ ማምረቻ መከፈት የኢትዮጵያን የውጭ ምርት ጥገኝነት ከመቀነስ ባሻገር ኢትዮጵያን በዘርፉ በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ የሚያደርግ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በሞጆ ከተማ የተገነባውን የግራንዴር ሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካን መርቀዋል። በሞጆ ከተማ በግራንዴር ሴራሚክ ማኑፋክቸሪንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር የተገነባው የሴራሚክና የፖርሲሌን ንጣፎች ማምረቻ ፋብሪካ፣ ከዕቅድና መሬት ዝግጅት እስከ ሙሉ ሥራ ማስጀመር የወሰደው ጊዜ ዘጠኝ ወራት ብቻ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ገልጿል። መሰረተ ልማቱ በ300,000 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያረፈው ይህ ፋብሪካ፣ የዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀና ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ መዋዕለ-ነዋይ የወጣበት ሲሆን፤ በኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር ጉዞ ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ ያመላከተ ክንውን መሆኑ ተመላክቷል። በአሁኑ ወቅት 60x60 የሴራሚክ ንጣፎችን በስፋት ማምረት የጀመረው ይህ ፋብሪካ፤ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ውስጥ የምርት ዓይነቶቹን በማስፋት የ80x80bg፣ 60x120፣ 70x140 እና 80x160 መጠን ያላቸውን የንጣፍ ዓይነቶች እንዲሁም የአውሮፓን የጥራት ደረጃ ያሟሉ የፖርሲሌን ምርቶችን ማቅረብ እንደሚጀምር ይጠበቃል። ለፋብሪካው ምርት የሚያስፈልጉት ጥሬ ዕቃዎች 80 በመቶ የሚሆነው ከፋብሪካው በ100 ኪሎ ሜትር ክበብ ውስጥ የሚገኙ በመሆኑ፣ ሙሉ በሙሉ የተቀናጀና ከአካባቢው ማኅበረሰብ ጋር የተሳሰረ የአቅርቦት ሰንሰለት መፍጠር ተችሏል። ኢትዮጵያ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት ባሳለፍናቸው ዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ ከ4.85 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማዳን በቻለችበት በዚህ ወቅት፤ የግራንዴር ሴራሚክ መከፈት የውጭ ምርት ጥገኝነትን የሚቀንስ ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ተወዳዳሪ እንድትሆን የሚያስችላትም ጭምር መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።
የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭት መሻሻል በሀዋሳ ከተማ የትራንስፖርትና ንግድ እንቅስቃሴን ይበልጥ አሳልጧል
May 23, 2026 109
ሀዋሳ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በሀዋሳ ከተማ የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭት በመሻሻሉ በትራንስፖርትና በንግድ እንቅስቃሴ ላይ ተፈጥሮ የነበረው ጫና መቀረፉን የከተማዋ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ አስታወቀ፡፡ መንግስት በመካከለኛው ምስራቅ በተፈጠረው ችግር ምክንያት ያጋጠመውን የነዳጅ አቅርቦት ችግር መቋቋም ያስቻሉ የመፍትሄ እርምጃዎችን መተግበሩ ይታወሳል፡፡ በሀዋሳ ከተማም መንግስት የወሰዳቸውን የመፍትሄ እርምጃዎች ተከትሎ የአቅርቦት ሁኔታው ወደነበረበት ተመልሷል። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አገና ኔቶ እንደገለጹት፤ የነዳጅ አቅርቦት መሻሻሉ በከተማዋ የትራንስፖርትና ንግድ እንቅስቃሴ የበለጠ እንዲሳለጥ አስችሏል።   በከተማው በመንግስት በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ነዳጅ በቁጠባ ጥቅም ላይ እንዲውል ሲደረግ መቆየቱንም አስታውሰዋል። በተለይም ለሕዝብ ትራንስፖርት፣ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች እንዲሁም ሸቀጣሸቀጦችን ለሚያጓጉዙ የጭነት ተሽከርካሪዎች ቅድሚያ በመስጠት የማዳረስ ሥራ ሲሠራ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ መንግስት ችግሩን ለመቅረፍ በወሰደው ቁርጠኛ አቋም አቅርቦቱ ወደ ነበረበት መመለሱንና በዚህም በትራንስፖርትና በንግድ እንቅስቃሴ ላይ ተጨባጭ ለውጥ መታየቱን ተናግረዋል። መምሪያውም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት የነዳጅ ስርጭቱ በአግባቡና በፍትሐዊነት እንዲዳረስ የክትትል ሥራውን አጠናክሮ መቀጠሉን ጠቁመዋል፡፡ ማደያዎች እና አሽከርካሪዎች በበኩላቸው ቀደም ሲል በነዳጅ አቅርቦት እጥረት ምክንያት በማደያዎች አካባቢ ረጅም ሰዓት ይሰለፉ እንደነበር አስታውሰው፣ አሁን ላይ ግን አቅርቦቱ ወደ ቀድሞ ሁኔታው መመለሱን ተናግረዋል፡፡   የሕዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት አሽከርካሪው ታረቀኝ ኢዩኤል ከሀዋሳ ወደ ተለያዩ ከተሞች የትራንስፖርት አገልግሎት እንደሚሰጡ ገልጸዋል። የነዳጅ አቅርቦቱ ውስን በሆነበት ወቅት እኛም ሆንን ማኅበረሰቡ ለከፍተኛ ችግር ተዳርገን ነበር፤ ነዳጅ በሳምንት አንድ ወይም ሁለት ጊዜ ብቻ የምናገኝበት አጋጣሚ ነበር ብለዋል። አሁን ላይ ግን ያለ ምንም እንግልት በቀላሉ ነዳጅ እያገኘን ማኅበረሰቡን በሚገባ ማገልገል ችለናል ሲሉ ገልጸዋል።   ሌላው በጭነት ትራንስፖርት ሰጪ ተሽከርካሪ ላይ ረዳት ሆነው እየሠሩ የሚገኙት ሲሳይ ጌጣ፤ በአብዛኛው እህልና ሸቀጣሸቀጦችን የማጓጓዝ ሥራ እንደሚሠሩ ተናግረዋል። አሁን የነዳጅ አቅርቦቱ በመሻሻሉ መደበኛ ሥራቸውን በተሻለ ሁኔታ ማከናወን መቻላቸውን አስረድተዋል።   በሀዋሳ ከተማ የታፍ ነዳጅ ማደያ ሥራ አስኪያጅ ያሬድ ካሱ፤ ነዳጅ በአግባቡ እየቀረበ እያገኘን ነው፤ እኛም ለተጠቃሚዎች ፍትሐዊ በሆነ መንገድ እያደረስን ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የግራንዴር ሴራሚክ ፋብሪካን መረቁ
May 23, 2026 148
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የግራንዴር ሴራሚክ ፋብሪካን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሴራሚክ ፋብሪካው የአምራች ኢንዱስትሪ ልማት ጉዞ አካል እና የ“ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ እመርታ ትልቅ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ቁልፍ ሀገራዊ ፋይዳ ያላቸውን መሰል ፋብሪካዎች ግንባታ፣ ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንቶችን በመሳብ በመላ ሀገሪቱ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በተግባር ያረጋገጠ ነው ብለዋል። ‎ ‎​ፋብሪካው የዓለም ዓቀፍ ጥራትና ተወዳዳሪነት መስፈርቶችን የሚያሟሉ የሴራሚክ ምርቶችን የሚያቀርብ ሲሆን፣ ለምርቱ የሚያስፈልጉትን ጥሬ ዕቃዎች ከ80 በመቶ በላይ ከሀገር ውስጥ ዐቅም እንደሚያገኝ ጠቁመዋል። ይህ ስኬት ኢትዮጵያ የራሷን የተፈጥሮ ሀብትና እምቅ ጸጋ የመጠቀም ብቃቷን ከመገንባቱ ባሻገር፣ ከውጭ ገቢ ምርቶች ላይ ያለንን ጥገኝነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚቀንሰውም ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት።
መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭቱ የተሳለጠ እንዲሆን አስችሏል
May 23, 2026 126
አዳማ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭቱ የተሳለጠ እንዲሆን ማስቻሉን የአዳማ ከተማ አስተዳደር ንግድ ጽህፈት ቤት ገለጸ። በመካከለኛው ምስራቅ ተከስቶ የነበረውን ጦርነት ተከትሎ፣ በተለይም በነዳጅ ምርት አቅርቦት ላይ ዓለምአቀፍ ችግር አስከትሎ እንደነበር ይታወሳል። ይህ ችግር በኢትዮጵያ የነዳጅ አቅርቦት ላይ መስተጓጎል ፈጥሮ የነበረ ቢሆንም መንግሥት በአቅርቦትና ስርጭት ላይ አዲስ አሰራር ተግባራዊ በማድረግ ችግሩን ለማቃለል ጥረት አድርጓል። በዚህም የነበረውን ዓለም አቀፍ ችግር በመቋቋም ማለፍ የተቻለ ሲሆን፣ አሁን ላይ በተለያዩ ከተሞች የተረጋጋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት መኖሩን ለማወቅ ተችሏል። በኦሮሚያ ክልል አዳማ ከተማ አሁናዊ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱ ምን እንደሚመስል ኢዜአ የሚመለከታቸውን አካላት፣ የነዳጅ ማደያዎችንና አሽከርካሪዎችን አነጋግሯል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ንግድ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ጢሎ ዱግዳ፤ በነዳጅ አቅርቦት ላይ አጋጥሞ የነበረውን ችግር ለመቋቋም በከተማ አስተዳደሩ የነዳጅ ስርጭት ግብረ ኃይል ተቋቁሞ፣ የነዳጅ ስርጭቱ ፍትሃዊ እና ተደራሽ እንዲሆን መስራቱን አንስተዋል። በመሆኑም አሁን ላይ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ችግር የሌለ በመሆኑ ጥሩ አገልግሎት እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል። በከተማዋ በሚገኙ 19ኝ ማደያዎች በቂ የነዳጅ አቅርቦት መኖሩን ገልጸው፣ በዚህም ተገልጋዮች ካለምንም እንግልት እየተጠቀሙ መሆኑንና የእንቅስቃሴ ችግር አለመኖሩን አንስተዋል። በከተማዋ ቀደም ሲል ህገወጥ የነዳጅ ዝውውርን ለመግታት በተደረገ ቁጥጥር 6ሺህ ሊትር ናፍጣና 6ሺህ ሊትር ቤንዚን መያዙን አስታውሰው፣ ህግ የማስከበር ስራ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል ብለዋል። በከተማዋ ከሚገኙ ነዳጅ ማደያዎች መካከል የኖክ ነዳጅ ማደያ ስራ አስኪያጅ ግዛው አበበ እና የአፍሪካ ቁጥር 1 ነዳጅ ማደያ ስራ አስኪያጅ ኮሚኒስት ወንድሙ፤ ቀደም ሲል በነዳጅ አቅርቦት ላይ የነበረው ችግር በመፈታቱ ደንበኞች በአግባቡ እየተስተናገዱ መሆኑን ገልጸዋል። ከአሽከርካሪዎች መካከል ጌቱ ተስፋዬ እና አሸናፊ አለሙ፤ በነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ላይ የነበረበው ችግር በመፈታቱ አሁን ላይ የተረጋጋ ሁኔታ እንዳለ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተግዳሮቶችን በጽናት በማለፍ በስኬት ጎዳና ላይ ይገኛል
May 22, 2026 608
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚያጋጥሙትን ተግዳሮቶች በጽናት በማለፍ በስኬት ጎዳና ላይ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ እና የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓል ማጠቃለያ መርሐ-ግብር አካሂዷል። በማጠቃለያው መርሐ-ግብር ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ እንግዶች ታድመዋል።   የቦርድ ሰብሳቢው ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ በመድረኩ ባደረጉት ንግግር፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሀገሪቱን ለዓለም የሚያስተዋውቅ ብርቅዬ ተቋም መሆኑን ገልጸዋል። አየር መንገዱ በሚሰጠው የላቀና ዘመናዊ አገልግሎት ምክንያት፣ ከበርካታ ዓለም አቀፍ ተቋማት በየዘመኑ ከፍተኛ እውቅና እየተሰጠው እንደሚገኝም ጠቁመዋል። አየር መንገዱ በየጊዜው የሚያጋጥሙትን የተለያዩ ተግዳሮቶች በጽናት በማለፍ ሁልጊዜም በስኬት ጎዳና ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ተቋሙ ከአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድነት ባለፈ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪነቱን ይበልጥ ለማሳደግ ስትራቴጂ ቀርጾ በስፋት እየሠራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት መንግሥት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት በተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ ሥራዎች አየር መንገዱ ስኬቶቹን አጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም ተቋሙ ለበለጠና ለላቀ ስኬት በከፍተኛ ቁርጠኝነት እንደሚሠራ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዓድዋ ድል ቀጥሎ አፍሪካውያንን ያስተሳሰረ የስኬትና የመቻል ዓርማ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 22, 2026 375
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዓድዋ ድል ቀጥሎ አፍሪካውያንን ያስተሳሰረ የስኬትና የመቻል ዓርማ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓል ማጠቃለያ መርሐ-ግብር አካሂዷል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ በሺህ ዘመናት ታሪኳ ተቋማትን በመመሥረትና በማጽናት እምብዛም ሳይሳካላት መቆየቷን አስታውሰዋል።   በዘመናዊ ታሪክ ከገጠሟት ስብራቶች መካከል የተቋማት ስብራት እንደሆነ ጠቅሰው፤ በፈተና ውስጥ ወጀቡን በማለፍ የኢትዮጵያን ስምና ሰንደቅ ዓላማ ከፍ አድርገው ታሪክ እየሠሩ የተጓዙ ተቋማት እንዳሏትም ተናግረዋል። በዚህ ረገድ ግንባር ቀደሙ የኢትዮጵያ አየር መንገድ መሆኑን ጠቅሰው፤ አየር መንገዱ ከዓድዋ ድል ቀጥሎ አፍሪካውያንን ያስተሳሰረና ያኮራ ተቋም መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የአፍሪካ የስኬት ተምሳሌት እና የመቻል ዓርማ ነው ብለዋል። የዘመናዊቱ አፍሪካ ታሪክ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ታሪክ ጋር የተሳሰረ ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለአፍሪካ ችግሮች ቀድሞ ደራሽ መሆኑንም አንስተዋል። በኮቪድ-19 ወረርሺኝ ወቅት ለሰው ልጅ ሕይወት እጅግ አስፈላጊ የሆኑ የሕክምና ቁሳቁሶችን በዓለም ዙሪያ በማጓጓዝ የበኩሉን ማበርከቱንም አውስተዋል።   የኢትዮጵያ አየር መንገድ በብዙ ፈተናዎች ውስጥ ለስኬት እንዲበቃ መሪዎቹና ሠራተኞቹ የከፈሉት ዋጋ በታሪክ የሚጠቀስ መሆኑን በአጽንኦት ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ በማስገባት፣ የሥራ ዕድል በመፍጠር፣ የኢትዮጵያን ወጪ ንግድ በመደገፍ፣ ሀገራችንን በአቪዬሽን መሠረተ ልማት ከፍ በማድረግ፣ የቱሪዝም ዘርፉን በማገዝ፣ እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት 80 ዓመታት ያስመዘገበው ዕድገት በተከታታይ ስኬቶች የታጀበ መሆኑን በማንሳት፤ ከጃን ሜዳ እስከ ቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ የደረሰውን ዕድገትም አድንቀዋል። ከኢትዮጵያውያን አልፎ መላው የጥቁር ሕዝብ በአየር መንገዳችን ይኮራል ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አየር መንገዱ ለቀጣይ ስኬቱ በሚያደርገው ጉዞ መንግሥት መሪም ደጋፊም ሆኖ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድን የሰማንያ ዓመት የአቪዬሽን ታሪክ የሚዘክር ቋሚ ዐውደ ርዕይ እንደሚያስፈልግም ጠቁመዋል። ዘመናዊት ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ መሠረት ከጣሉ እና ቁልፍ ሚና ከተጫወቱ ተቋማት መካከል አንዱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ መሆኑን በድጋሚ ማረጋገጥ እንደሚገባ ተናግረዋል። በቀጣይም በአቪዬሽን ኢንዱስትሪው ውስጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ አሉ ከሚባሉ ሀገራት ተርታ ለመሰለፍ ተቋሙ በትጋት መስራት እንዳለበትም ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የመጀመሪያ በረራውን በ1938 ዓ.ም በአስመራ በኩል ወደ ካይሮ ማድረጉ ይታወሳል።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስደማሚ ስኬቶችን አስመዝግቧል
May 22, 2026 339
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፉት የለውጥ ዓመታት አስደማሚ ስኬቶች ማስመዝገቡን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓል ማጠቃለያ መርሐ-ግብር አካሂዷል። በየማጠቃለያ መድረኩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢና የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።   የግሩፑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው በማጠቃለያው መድረክ ላይ እንዳሉት፤ የምሥረታ በዓል መርሐ-ግብሩ "ዘመን ተሻጋሪ ስኬት" በሚል መሪ ኃሳብ ሲካሄድ መቆየቱን አስታውሰዋል። አየር መንገዱ ወደ ካይሮ "አንድ" ብሎ የጀመረው ታሪካዊ ጉዞ ዛሬ ላይ በአምስት አህጉራት 145 መዳረሻዎች እንዲኖሩት ማድረጉን ገልጸው፤ በአሁኑ ወቅት ተቋሙ የ147 ዘመናዊ አውሮፕላኖች ባለቤት መሆኑን ጠቁመዋል። በተጨማሪም በአመት ከ20 ሚሊየን በላይ መንገደኞችን በማጓጓዝ በአፍሪካ ግንባር ቀደም አየር መንገድ ለመሆን መብቃቱን ዋና ሥራ አስፈጻሚው ገልጸዋል። ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት የተመዘገቡትን አስደማሚ ስኬቶች በቁጥር ሲያብራሩም፤ በዚህ ጊዜ ውስጥ የአዳዲስ አውሮፕላኖች ቁጥር በ47 በመቶ ማደጉን ጠቁመዋል። አየር መንገዱ የሚያጓጉዘው የደንበኞች ቁጥር በ97 በመቶ፣ ዓመታዊ ገቢው በ121 በመቶ ማደጉንና ትርፉም በሦስት እጥፍ መጨመሩን አንስተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በማይናወጥ ጠንካራ መሠረት ላይ መገንባቱን ጠቁመው፤ በቀጣይም እነዚህን የስኬት እሴቶቹን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።
የከተሞች ትንሣኤ፡-  የልማት አሻራ፣ የዕድገት እጥፋትና የነገው ብሩህ ተስፋ
May 22, 2026 196
የከተማ ልማት ዕሳቤና ፖሊሲ የከተማውን ኅብረተሰብ መሠረታዊ ጥያቄዎች የሚመልስ ሥርዓት መገንባትን ቀዳሚ ያደረገ ነው። ከተሞችን ተስማሚ የመኖሪያ ሥፍራ ብቻ ሳይሆን አካታች፣ ስማርት እና ለኑሮ ምቹ የሆኑ የብልፅግና ማዕከላት የማድረግ ራዕይ ተይዟል። ዋነኛ ግቡም ከተሞችን የሁሉም ዜጎች የጋራ መኖሪያ ማድረግ፣ ፍትሓዊ የቤት አቅርቦትን ማረጋገጥ እና የዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ማዕከላት ማድረግ ነው። መንግሥት “መደመርን” እንደ መንገድ በመውሰድ የከተሞችን ተግዳሮት ወደ ልማት ዕድሎች የመቀየር ስትራቴጂን ተግባራዊ አድርጓል። በዚህም የገጠር-ከተማ ትሥሥርን በማጠናከርና የተሰባሰበ አሰፋፈር ያላቸውን ከተሞች በመፍጠር ለነገው ትውልድ የምትመች አገር የመገንባት ታላቅ ሥራ ተጀምሯል። የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና የማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች ለዜጎች በተሻለ ቅልጥፍና እንዲቀርቡ የተደረገ ቢሆንም፣ ከተሞችን በተቀናጀ የረጅም ዘመን ፕላን የመምራት ውስንነት፣ የመረጃ አያያዝ ችግሮች እና ገቢን በሥርዓት አለመሰብሰብ አሁንም የሚታዩ ክፍተቶች ናቸው ። እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍም ተቋማዊ ሪፎርሞች በቁርጠኝነት እየተከናወኑ ይገኛሉ። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በከተማ ልማት ዘርፍ ሞዴል ሥራዎች በፍጥነትና በጥራት ተከናውነዋል። ለአብነትም መዲናችን አዲስ አበባ በወንዝ ዳርቻ እና በኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች አማካይነት የአፍሪካ የከተማ ልማት ሞዴል እንድትሆን ተደርጋለች። የጫካ ኢኮ-ስማርት ሲቲ ፕሮጀክት አረንጓዴ ኢኮኖሚንና ዘመናዊ መሠረተ ልማትን ያዋሐደ ትልቅ ስኬት ሲሆን፣ የጣና ዳርቻ፣ የጅማ የሥነ-ምኀዳርና የሐረር የኮሪደር ልማት ሥራዎች የመንግሥትን ሁለንተናዊ የለውጥ ዐቅም አሳይተዋል። ሕገ ወጥ የመሬት ወረራን ለመከላከል በተሠሩ ሥራዎች በ2017 በጀት ዓመት ብቻ 206 ሺህ ሕገ ወጥ ይዞታዎች ወደ ሕጋዊ ሥርዓት እንዲገቡ የተደረገ ሲሆን፣ ለ115 ሺህ ሰነድ-አልባ ይዞታዎች ሰነድ ተዘጋጅቷል። ባለፉት 5 ዓመታት በመንግሥት፣ በሪል ስቴት አልሚዎች እና በግል ቤት ሠሪዎች ትብብር ከ1.1 ሚሊዮን በላይ ቤቶች ተገንብተዋል። በተጨማሪም ማኅበረሰብን በማስተባበር 166,207 የዐቅመ ደካማ ቤቶች ተገንብተው ተላልፈዋል። ከደረጃ በታች የሆኑ የከተማ ቤቶች ድርሻም በ2013 ከነበረበት 75 በመቶ በ2017 ወደ 52 በመቶ ዝቅ እንዲል ተደርጓል። በሚቀጥሉት ዓመታት የከተማ መሬትን ምርታማነት ለመጨመር የይዞታ ማረጋገጫ ሥርዓት የሚጎለብት ሲሆን፣ የመሬት አያያዝ እና አጠቃቀም ይበልጥ ፍትሓዊ እንዲሆን እቅድ ተይዟል ። በከተሞች የሚታየውን የመኖሪያ ቤት እና የሥራ አጥነት ችግር ለመፍታት በትኩረት የሚሠራ ሲሆን፣ በሚቀጥሉት ዓመታት 2.2 ሚሊዮን ቤቶች እንዲገነቡ ይደረጋል። በከተሞች ያለው የቤት ሽያጭ እና የቤት ኪራይ አሠራር ገበያ-መር ሆኖ ፍትሓዊ የገበያ ሥርዓትን እንዲከተል ማድረግ ያስፈልጋል ። ከተሞች ከበካይ ነገሮች የጸዱ እንዲሆኑ ከከተማ ይዞታ ውስጥ 30 በመቶው የአረንጓዴ ልማት ቦታ ሆኖ እንዲጠበቅ እየተሰራ ነው ። የመንገድ፣ የትራንስፓርት፣ የንጹሕ ውኃ እና የመብራት አቅርቦት ተደራሽነትን ለማሳደግ ሰፊ ርብርብ ማድረግ ይገባል ።
በዜጎች ሕይወት ላይ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡ ፕሮጀክቶችን አጠናክረን እንቀጥላለን - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 22, 2026 266
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር 24/7 በመሥራት በዜጎች ኑሮ ላይ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡና ማኅበረሰቡ ጤናማ በሆኑ አካባቢዎች አገልግሎት ማግኘት የሚችልባቸውን ፕሮጀክቶች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ የዓድዋ የገበያ ማዕከል እና የትራንስፖርት ተርሚናልን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል፡፡   ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ መንግሥት አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብ እና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን በሚመጥን መልኩ የመሠረተ ልማት ግንባታ ሥራዎችን አጠናክሮ ቀጥሏል። ከተማ አስተዳደሩ ቃል በገባው መሠረት ዜጎች ምቹ በሆነ አካባቢ የተቀላጠፈ አገልግሎት የሚያገኙባቸው በርካታ መሠረተ ልማቶች መገንባታቸውን አንስተዋል። ለአብነትም ምቹ የእንቅስቃሴ መንገዶችን ማስፋፋት፣ ሕዝቡ በጥሩ ሁኔታ ላይ ሆኖ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚያገኝባቸውን ተርሚናሎች መገንባት እንዲሁም ዘመናዊ የመሸጫ የንግድ ሱቆችን ማጠናከር ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዛሬው ዕለትም የሕዝብን ክብር በሚመጥን መልኩ የተገነባው የዓድዋ የገበያ ማዕከልና የትራንስፖርት ተርሚናል መመረቁን የገለጹት ከንቲባዋ፤ ይህም የተቀናጀ አገልግሎትን ለማኅበረሰቡ ለመስጠት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር አስታውቀዋል። ከተማ አስተዳደሩ 24/7 በመሥራት በዜጎች የዕለት ተዕለት ሕይወት ላይ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡ ፕሮጀክቶችን በመሥራት ትጉህነቱን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዲዛይንና ግንባታ ሥራዎች ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር አያልነሽ ሀብተማርያም በበኩላቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ የሀገሪቱን የልማት ጉዞ የሚመጥኑና ለትውልድ አኩሪ የሆኑ በርካታ ፕሮጀክቶችን ገንብቶ ለአገልግሎት ማብቃቱን ገልጸዋል። በዛሬው ዕለት ለንግድ እንቅስቃሴ መዘመንና ለትራፊክ ፍሰት መሳለጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ የዓድዋ የገበያ ማዕከል እና የትራንስፖርት ተርሚናል፤ ሌሊትና ቀን በመሥራት ለአገልግሎት ክፍት መደረጉን ጠቁመዋል። ይህ የዓድዋ የገበያ ማዕከል እና የትራንስፖርት ተርሚናል ፕሮጀክት በውስጡ በርካታ የተሽከርካሪ ማቆሚያዎችን፣ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያዎችን፣ የተለያዩ ምርቶች መሸጫ ሱቆችንና ሌሎችንም ዘመናዊ የአገልግሎት መስጫዎችን እንደያዘ ጠቅሰዋል።   የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ ያብባል አዲስ በበኩላቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ የትራንስፖርት ዘርፉን ለማሳደግ ዘርፈ-ብዙ የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ እየሠራ መሆኑንና የዛሬው ተርሚናል ምርቃትም የዚህ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት የተከናወኑ የከተማ ልማት ሥራዎች ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ አድርገዋል
May 22, 2026 149
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የተከናወኑ የከተማ ልማት ሥራዎች ከተሞችን ለነዋሪዎች የተመቹ፣ ለጎብኚዎች ደግሞ ውብና ሳቢ እንዲሆኑ ማስቻሉን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ገለጹ። የከተማ ልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር ዜጎችን ከተረጂነት ወደ አምራችነት በማሸጋገር ረገድ በአፍሪካ ደረጃ አርአያነት ያለው መሆኑን ጠቅሰዋል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በርካታ የከተማ ልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። ለከተሞች ልማት ትኩረት በመሰጠቱ ለነዋሪዎች ምቹ፣ ለጎብኚዎች ደግሞ ውብና ሳቢ እንዲሆኑ መደረጉን ገልጸዋል። ለአብነትም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተተገበረው የኮሪደር ልማት፣ የከተሞችን ገጽታ ሙሉ በሙሉ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹና ተስማሚ የአኗኗር ከባቢ መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡ የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክቶች አዲስ አበባን የአፍሪካ ተምሳሌትና ለቱሪዝም ፍሰት ምቹ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ ይህ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተመዘገበው ታላቅ የልማት ስኬት፣ የነዋሪዎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በዘላቂነት የሚያረጋግጡ ዘመናዊ መሠረተ ልማቶችን በስፋት ማካተት መቻሉን ጠቅሰዋል። ጥራት ያላቸው ዘመናዊ የእግረኛ መንገዶችን በመገንባት ዜጎች በነፃነትና በደኅንነት እንዲንቀሳቀሱ ያስቻለ ሲሆን፣ ለተሽከርካሪዎችም ምቹና ደረጃቸውን የጠበቁ መንገዶች በመስራት የትራፊክ ፍሰቱ በእጅጉ እንዲቃለል ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም ፕሮጀክቱ የአካባቢ ጥበቃን፣ የአረንጓዴ ልማትንና የነዋሪዎችን ጤናማ የአኗኗር ዘይቤ ታሳቢ ያደረገ መሆኑ ተናግረዋል፡፡ ይህ ሁለንተናዊ የከተማ ልማት ሥራ የዜጎችን የዕለት ተዕለት ሕይወት በማሻሻል ረገድ የላቀ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡ መንግሥት ለከተሞች በሰጠው ትኩረት ለውጥ ከተመዘገበባቸው የልማት ሥራዎች አንዱ የሆነው የከተሞች ልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር፣ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ያሉ ዜጎችን ሕይወት በተግባር መቀየሩን ተናግረዋል። መርሃ ግብሩ በሰማንያ ስምንት ከተሞች የሚተገበርና 2 ነጥብ 5 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎችን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። ከተጠቃሚዎቹ መካከል 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚበልጡት ተመርቀው ወደ አምራችነት መሸጋገራቸውን ጠቅሰው፤ ቀሪዎቹ ደግሞ በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ውስጥ እንደሚሸጋገሩ አብራርተዋል። ይህ አሠራር ዜጎች በኢንተርፕራይዝ ደረጃ በመደራጀት ራሳቸውን ከመደገፍ ባለፈ፣ ለሌሎችም ተጨማሪ የስራ ዕድል እንዲፈጥሩ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው የከተማ ልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር ስኬታማነት በአፍሪካ ደረጃ ሞዴል የሆነና ሌሎች ሀገራትም ተሞክሮ እየወሰዱበት ያለ መሆኑን ተናግረዋል።
በፓርኩ ያለው የተሟላ መሰረተ ልማትና በመንግስት የሚደረገው ድጋፍ ባለሀብቱን መሳብ እያስቻለ ነው
May 22, 2026 131
ሀዋሳ፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ በይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ ያለው የተሟላ መሰረተ ልማትና በመንግስት የሚደረገው ድጋፍ አልሚ ባለሀብቶችን እየሳበ መሆኑ ተገለጸ። በፓርኩ የአዳዲስ ፋብሪካዎች ምረቃና የዕውቅና መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡ በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ሙዝና ቡናን በዘመናዊ መልኩ ዕሴት ጨምረው ለዓለም ገበያ የሚያቀርቡ ሁለት አዳዲስ ፋብሪካዎች በይፋ ሥራ ጀምረዋል።   በመርሃ ግብሩ የተገኙት የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ኃላፊና የፓርኩ የቦርድ ሰብሳቢ መምሩ ሞኬ፤ የኢኮኖሚው መሰረት የሆነውን የግብርና ምርት ዕሴት ጨምረው ለውጭ ገበያ ለሚያቀርቡ ኢንዱስትሪዎች መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። በዚህ በኩል የይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ በአጭር ጊዜ ውስጥ በምርቶች ላይ ዕሴት በመጨመር ውጤታማ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለበርካታ የአካባቢው አርሶ አደሮችና ወጣቶች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የውጭ ምንዛሪን በማስገኘት በኩል ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ለዚህ ደግሞ አስፈላጊው መሰረተ ልማት የተሟላለት ፓርኩ ለባለሀብቶች ምቹ መሆኑ ዋነኛ ምክንያት መሆኑን አብራርተዋል።   የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኃይሉ የተራ፤ ፓርኩ ሥራ ከጀመረባቸው ባለፉት አምስት ዓመታት ወዲህ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በውጭ ምንዛሪ ግኝት፣ በተኪ ምርት፣ በገበያ ትስስርና በሥራ ዕድል ፈጠራ ከፍተኛ ውጤት እያስገኘ ነው ብለዋል። በፓርኩ የግብርና ምርቶችን በማቀነባበር ሥራ ላይ ለመሰማራት ዛሬ ሥራ የጀመሩትን ጨምሮ በአጠቃላይ 10 ኩባንያዎች በምርት ሂደት ላይ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በዚህም እስካሁን ከ26ሺህ ለሚልቁ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቅሰው፤ ፓርኩ ባለው የመሰረተ ልማት ምቹነት፣ በመንግስት ቀጣይነት ያለው ድጋፍና ክትትል ታክሎበት የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል። በዕለቱ በይፋ ሥራ ከጀመሩት ፋብሪካዎች መካከል የኤፔክስ ማኑፋክቸሪንግና ትሬዲንግ መስራችና ዋና ሥራ አስኪያጅ መስፍን ተፈራ ኩባንያቸው ሙዝን በዘመናዊ መንገድ በችፕስ መልክ ለገበያ ለማቅረብ ስራ መጀመሩን ተናግረዋል። የፋብሪካው ሥራ መጀመር በክልሉና በአጎራባች አካባቢዎች በስፋት በሙዝ አምራችነት ለተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጨማሪና አስተማማኝ ገቢ ይዞ መምጣቱን ጠቅሰው፤ በአሁኑ ወቅት ከ60ሺህ ከሚሆኑ አምራቾች ጋር የገበያ ትስስር መፈጠሩን አመልክተዋል። ኩባንያው ምርቶቹን ከሀገር ውስጥ ገበያ ባለፈ ወደ ውጭ እንደሚልክም ገልጸዋል።   ሌላው በቡና ማቀነባበር ሥራ ላይ የተሰማራው የቻይናው 'መይመይ ኮፊ ፕሮሰሲንግ' ኩባንያ ተወካይ ሚስተር ጄ ሶን፤ በፓርኩ በተፈጠረው ምቹ ሁኔታና መሰረተ ልማት ተስበው ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። ፋብሪካው ቡናን ከአርሶ አደሩ ማሳ ቀጥታ በመረከብ፤ ማጠብና መፍጨት ጀምሮ የተጠናቀቀ ዝግጁ ቡና ለዓለም አቀፍ ገበያ እስከማቅረብ ድረስ ያለውን ሙሉ ሂደት እዚያው ፓርኩ ውስጥ እንደሚያከናውን ገልጸዋል። በዕለቱ ዕውቅና ከተሰጣቸው ባለሀብቶች መካከል የ'ጎልደን' የአቮካዶ ዘይት ፋብሪካ ባለቤት ወይዘሮ ይርጋለም አስፋው ፋብሪካው ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ ብቻ 16 ኮንቴይነር የአቮካዶ ዘይት ምርት ወደ ውጭ ሀገር መላክ ችሏል ብለዋል። ዛሬ የተሰጣቸው ዕውቅና በቀጣይ ይበልጥ ጠንክረው እንዲሰሩ ትልቅ መነቃቃት የፈጠረላቸው መሆኑን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መካከል ያለው የላቀ ትብብር ለኢትዮጵያውያን ሰፊ የሥራ ዕድል ፈጥሯል 
May 22, 2026 143
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መካከል ያለው የላቀ ትብብር ለኢትዮጵያውያን ሰፊ የሥራ ዕድል እየፈጠረ መሆኑን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምሥራቅ፣ የእስያና ፓስፊክ ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር ጄነራል አምኃ ኃይለጊዮርጊስ ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መካከል ያለውን የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር ለማጠናከር ያለመው የዱባይ-ኢትዮጵያ ቢዝነስ ትስስር ፎረም በአዲስ አበባ ተካሂዷል፡፡   በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምሥራቅ፣ የእስያና ፓስፊክ ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር ጄነራል አምኃ ኃይለጊዮርጊስ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የዱባይ-ኢትዮጵያ ቢዝነስ ትስስር ፎረም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ትብብር ለማጠናከር ወሳኝ ነው፡፡ ኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ያላቸው ሁለንተናዊ ግንኙነት እየጎለበተ መምጣቱን ገልጸው፤ ፎረሙ የጋራ ተጠቃሚነትን ያረጋግጣል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ስትራቴጂያዊ የንግድና ኢንቨስትመንት መዳረሻ ናት ያሉት ምክትል ዳይሬክተር ጄነራል አምኃ፤ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ ወሳኝ አጋር መሆኗንም ገልጸዋል፡፡ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ የውጭ ንግድ መዳረሻ መሆኗን ገልጸው፤ 169 ኩባንያዎች በኢትዮጵያ የተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ተሰማርተው ይገኛሉ ብለዋል፡፡ እንደ አውሮፓውያን የዘመን ቀመር በ2018 ጀምሮ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው ግንኙነት በጥልቀትና በስፋት እያደገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ትብብሩም የሁለቱ ሀገራት የጋራ ብልጽግናን እውን ሊያደርግ በሚችል የጋራ እሴቶች ላይ የተመሠረተ መሆኑን አንስተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ብዝኃና እምቅ የንግድና ኢንቨስትመንት አቅም፣ ለኢንቨስትመንት የተመቹ አሠራሮች እንዳሏት በማንሳት፤ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ኩባንያዎች ዕድሉን ሊጠቀሙበት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ በኢትዮጵያ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ኤምባሲ የኢኮኖሚ፣ ፖለቲካና ሚዲያ ክፍል ኃላፊ ራሼድ አብዱላ አልሸሂ፤ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች የምትከተለው የዓለም አቀፍ የቢዝነስ ትስስር ሞዴል ኢትዮጵያንም ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል፡፡   በሌላ በኩል ሀገሪቱ ያላትን ሰፊ የገበያ አማራጭና እየተገበረች ያለውን የኢኮኖሚ ማሻሻያ በመጥቀስ፣ ለንግድና ኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎችን እየፈጠረች መሆኑን አስገንዝበዋል። የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች በታዳሽ ኃይል፣ በግብርናና ኢንዱስትሪ እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ትብብር የምታጠናክርበት መድረክ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ኢንጂነር አበበ ጉርሜሳ በበኩላቸው፤ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ለምክር ቤቱ አባል ኩባንያዎች ዋነኛ መዳረሻና መገኛ መሆኗን ገልጸዋል፡፡   የዱባይ ኩባንያዎች በዲጂታል አገልግሎት፣ በቱሪዝምና በሌሎችም ዘርፎች ያላቸው ተሳትፎ ለሁለቱ ሀገራት ኩባንያዎች ትብብር መሠረት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አበባና የዱባይ የቢዝነስ ኩባንያዎች በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ በጋራ በመሰማራት ትብብራቸውን እንዲያጠናክሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በክልሉ በለውጡ ዓመታት ሕዝቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተጠናቀው ለአገልግሎት በቅተዋል
May 22, 2026 120
ሸገር፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ባለፉት የለውጥ ዓመታት ሕዝቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ሰዓዳ አብዱረህማን ገለጹ። በሸገር ከተማ አስተዳደር በኮዬ ፈጬና በገላን ክፍለ ከተሞች የተገነቡ የ“ቡኡራ ቦሩ” ቅድመ መደበኛ እና የአንደኛ ደረጃ ሞዴል ትምህርት ቤቶች፣ የንጹህ መጠጥ ውኃ እንዲሁም የሕዝብ መናፈሻ ፓርኮች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል።   በምርቃቱ ሥነ ሥርዓት ላይ የተገኙት የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ሰዓዳ አብዱረህማን እንደገለጹት፤ በክልሉ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የሕዝቡን መሠረታዊ ጥያቄዎች የመለሱ በርካታ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት በመገንባታቸው የሕብረተሰቡ ተጠቃሚነት ሊረጋገጥ ችሏል። በተለይም በእውቀትና ቴክኖሎጂ የዳበረ፣ አገር ተረካቢ ትውልድ ለማፍራት ጊዜው የሚጠይቀውን ዘመናዊ ትምህርት ተደራሽ ከማድረግ አኳያ ሰፊ ሥራ መሠራቱን አብራርተዋል። በሸገር ከተማ በኮዬ ፈጬና ገላን ክፍለ ከተሞች ዛሬ የተመረቁት ትምህርት ቤቶች፣ የመጠጥ ውኃና የፓርክ ፕሮጀክቶች የዚሁ ሰፊ እንቅስቃሴ ማሳያ መሆናቸውን የገለጹት አፈ ጉባኤዋ፤ መምህራን ትውልዱን በማነጽ ረገድ የበኩላቸውን ኃላፊነት መወጣት እንዳለባቸው አሳስበዋል። ሕዝቡም ከመንግሥት ጎን በመሆን ሁለንተናዊ ተሳትፎውን አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ጥሪ አቅርበዋል። የሸገር ከተማ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤ በሸገር ከተማ ባለፉት ሦስት ዓመታት የከተማዋን ሀብት በአግባቡ በማስተዳደር የነዋሪውን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት ተደርጎ መሠራቱን ገልጸዋል።   በከተማዋ በርካታ የልማት ፕሮጀክቶችን በመገንባት የሕብረተሰቡ የልማት ጥያቄ በተሟላ መልኩ እየተመለሰ መሆኑንም አክለዋል። ባለፉት ሦስት ዓመታት በከተማዋ መሠረተ ልማቶችን ከመዘርጋት፣ የከተማዋን ገቢ ከማሳደግ፣ የጤና ተቋማትን ከመገንባትና ኢንቨስትመንትን ከማስፋፋት አኳያ ተጨባጭ ሥራዎች መከናወናቸውን ከንቲባው አንስተዋል። በተለይም የከተማዋን አርሶ አደር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ሼዶችና የገበያ ማዕከላት ግንባታቸው ተጠናቀው ለአርሶ አደሮቹ መተላለፋቸውን ተናግረዋል። በተያዘው በጀት ዓመት ከተማ አስተዳደሩ 448 የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለመገንባት አቅዶ እስካሁን 338 የሚሆኑ ፕሮጀክቶች ማጠናቀቅ መቻሉን ገልጸዋል።   የከተማ አስተዳደሩ ሳይመሠረት በፊት በትምህርት ገበታ ላይ የነበሩ ተማሪዎች ቁጥር ከ100 ሺህ የማይበልጥ የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ላይ ከ400 ሺህ በላይ ማድረስ መቻሉን ከንቲባው ገልጸዋል። በተጨማሪም በገላን ክፍለ ከተማ ተገንብቶ የተመረቀው የንጹህ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት ከ33 ሺህ በላይ የአካባቢው ነዋሪዎችን ንጹሕ የመጠጥ ውኃ ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑ ታውቋል።   የኮዬ ፈጬ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ኩመላ ሂርጳ፤ በክፍለ ከተማው በበጀት ዓመቱ የታቀዱ 25 የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን በመንግሥት በጀትና በሕዝብ ተሳትፎ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ዛሬ በቱሉ ዲምቱ ወረዳ ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት ትምህርት ቤቶች በክፍለ ከተማው ከተከናወኑት ስኬታማ ሥራዎች መካከል ተጠቃሽ መሆናቸውን የገለጹት ኃላፊው፤ ፕሮጀክቶቹ የትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ የአካባቢው ማኅበረሰብ ልጆቹን በአቅራቢያው ለማስተማር እንደሚያስችለው ገልጸዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጠናክሮ ቀጥሏል
May 22, 2026 94
አምቦ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች በጥራትና በብዛት እየተገነቡ መሆናቸውን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በዞኑ ኤጀሬና ወልመራ ወረዳዎች የተገነቡ የኮሪደር ልማት፣ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ህንፃ እና ሌሎች የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል። በፕሮጀክቶቹ ምረቃ ስነ-ስርዓት ላይ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታን ጨምሮ የዞኑና የወረዳዎቹ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል። ዋና አስተዳዳሪው አቶ ዲዳ ጉደታ በወቅቱ እንደገለጹት፤ መንግስት የገባውን ቃል በመተግበር የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ እየመለሰ ይገኛል።   በዞኑም ባለፉት የለውጥ ዓመታት ለረጅም ጊዜ የህብረተሰቡ ጥያቄ ሆነው የቆዩትን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና የሌሎች ዘርፎች ጥያቄዎችን መመለስ መቻሉን ተናግረዋል። ወደፊትም የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች በጥራትና በብዛት የመገንባቱ ስራ ይቀጥላል ብለዋል። የኤጄሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አዱኛ ብሩ በበኩላቸው፤ በወረዳው ለአገልግሎት ከበቁ የልማት ፕሮጀክቶች መካከል የሁለት ኪሎ ሜትር የከተማ ኮሪደር ልማት፣ የወተት ላሞች እርባታና የከብት ማደለቢያ ማዕከላት እንደሚገኙበት ገልጸዋል።   በወረዳው ዛሬ ለምርቃት የበቁት እነዚህ ፕሮጀክቶች በህብረተሰቡ ተሳትፎና በመንግሥት በጀት በአጠቃላይ 122 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በተመሳሳይ የወልመራ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጋሪ በበኩላቸው፤ አካባቢው የበጋ ስንዴን ጨምሮ የተለያዩ የሰብል እህሎች በስፋት የሚመረቱበት መሆኑን ገልጸው፤ ዛሬ የተመረቀው የ13 ነጥብ 2 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ወረዳውን ከቀበሌዎች ጋር የሚያገናኝ በመሆኑ አርሶ አደሮች ምርታቸውን በቀላሉ ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እንደሚረዳቸው አስረድተዋል።   ዛሬ ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል የከብትና የዶሮ እርባታ ማዕከላት፣ ባለ ሶስት ወለል የወረዳ ፍርድ ቤት ህንፃ እና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተጨማሪ ክፍሎች ይገኙበታል ብለዋል። እነዚህ ፕሮጀክቶች በመንግሥት በጀትና በህብረተሰቡ ተሳትፎ በአጠቃላይ 250 ሚሊዮን ብር ወጪ የተሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። የወልመራ ወረዳ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ስሪኔሳ ኩማላ፤ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው ባለ ሶስት ወለል የፍርድ ቤት ህንጻ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋ የህግ አገልግሎት ለመስጠት ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ተናግረዋል።   የኤጀሬ እና የወልመራ ወረዳ ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ የልማት ጥያቄዎቻቸው ለብዙ ዓመታት መልስ ሳያገኙ መቆየታቸውን አስታውሰው፤ አሁን ላይ ለተገነቡላቸው ፕሮጀክቶች የተሰማቸውን ደስታ በመግለጽ አስፈላጊውን እንክብካቤ እንደሚያደርጉ አረጋግጠዋል።
መንግስት ሰላምን ከማስከበር ጎን ለጎን ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ተግባራትን አከናውኗል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
May 22, 2026 68
ባህርዳር፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል መንግስት ሰላምን ከማስከበር ጎን ለጎን ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ በርካታ የልማት ተግባራትን አከናውኗል ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለፁ። "ኢትዮጵያን ወደ ተምሳሌት ሀገር" በሚል መሪ ሃሳብ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫን አስመልክቶ ከባህርዳር ከተማ አስተዳደር ከተውጣጡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር የውይይት መድረክ ተካሄዷል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የለውጡ መንግስት ፕሮጀክቶችን በማቀድና ፈጥኖ በመጨረስ ለሀገሪቱ አዲስ ልምምድ አበርክቷል። በቱሪዝም፣ በማዕድን ፣ በግብርና ፣ በኢንዱስትሪና ሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች ተግባራዊ የተደረጉ ፕሮጀክቶችም ለአገር እድገት መሰረት የሆኑና የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ያረጋገጡ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለዚህም መላውን ህዝብ በማሳተፍ የክልሉን ሰላም ለማረጋገጥ የተደረገው ጥረት ውጤት እያስገኘ በመምጣቱ ለልማት ስራው ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አስረድተዋል። በቀጣይም ህዝቡን በማስተባበር በልማትና በሰላም ማስፈን ስራዎች ለማረባረብ እንደሚሰራ ጠቁመው ምርጫውን በሰላም ለማጠናቀቅ ህዝቡ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እንዲወጣም አሳስበዋል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ‎‎‎አቶ ጎሹ እንዳላማው በበኩላቸው፤ ሀገር ጸንታ የምትቀጥለውና የምትሻገረው የሚያጋጥሙ ችግሮችን በንግግርና በውይይት መፍታት ሲቻል ነው ብለዋል።   የሚገጥሙ ችግሮችን በውይይት እና በመግባባት መፍትሔ በመስጠት የሚካሄዱ የልማት ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ለማድረግ የጎላ ፋይዳ እንደሚኖረውም አስረድተዋል። ‎ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫም ፍፁም ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሁሉም ህብረተሰብ የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ብለዋል። ‎ምርጫውን ነፃ፣ ፍትሃዊ፣ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅና የባህር ዳር ከተማን ተመራጭ የቱሪዝም፣ የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ከተማ ለማድረግ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በመድረኩም የክልሉና የባህርዳር ከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሃገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶችና ሴቶች ታድመዋል።
በዞኑ ለመኸር ወቅት የተዘጋጀ ከ10 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ እየዋለ ነው
May 22, 2026 102
ደብረ ብርሃን ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ለመኸር ወቅት እርሻ ለምርት ማሳደጊያነት በአርሶ አደሮች የተዘጋጀ ከ10 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ጌታነህ ተክለማሪያም ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የተፈጥሮ ማዳበሪያ የአፈር ለምነትንና እርጥበትን በመጨመር ለምርት እድገት የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። በዚህም በዞኑ ለ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት በአርሶ አደሮች የተዘጋጀ ከ10 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑን ተናግረዋል። በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅቱ ከ363ሺህ በላይ አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን አመልክተዋል። እስካሁንም ሰባት ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ የሚሆነው የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማሳን ደጋግሞ በማረስ ከአፈር ጋር በመቀላቀል ጥቅም ላይ መዋሉን ተናግረዋል። በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅቱ ከተሳተፉ አርሶ አደሮች መካከልም አቶ ኩራ ተሾመ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት የተፈጥሮ ማዳበሪያን አዘጋጅተው በመጠቀማቸው የማሳቸው ለምነት መጨመሩ የሰብል ምርታቸውን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። ዘንድሮም የተፈጥሮ ማዳበሪያ በማዘጋጀት አንድ ሄክታር ተኩል መሬታቸውን በቢራ ገብስ፣ በአተርና ባቄላ ዘር ለመሸፈን እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። አርሶ አደር ገበየሁ ማንደፍሮ በበኩላቸው፤ ባለፉት አመታት የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘጋጅተው በመጠቀማቸው ምርታቸውን ከማሳደግ ባለፈ ለፋብሪካ ማዳበሪያ ግዥ የሚያወጡትን ወጭ መቀነስ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። ዘንድሮም ለመኸር ወቅት እርሻ የሚሆናቸውን የተፈጥሮ ማዳበሪያ ከቅጠላቅጠል፣ ከእንስሳትና ሰብል ተረፈ ምርት በማዘጋጀት ሁለት ሄክታር መሬታቸውን በተለያዩ ሰብሎች በዘር የመሸፈን ስራ መጀመራቸውን ተናግረዋል። በዞኑ በ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት ከ563 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰብል በማልማት 20 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑ ታውቋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም