ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ኢትዮጵያ በ28ኛው የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ላይ የአረንጓዴ አሻራና ሌሎችም ተሞክሮዎቿን ታስተዋውቃለች
Nov 30, 2023 38
አዲስ አበባ፤ ህዳር 20/2016(ኢዜአ፦ኢትዮጵያ በዱባይ በሚካሔደው 28ኛው የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ላይ የአረንጓዴ አሻራና ሌሎችንም ተሞክሮዎቿን ለዓለም እንደምታስተዋውቅ የፕላንና ልማት ሚኒስትሯ ዶክተር ፍጹም አሰፋ ገለጹ። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባዔ (ኮፕ 28) በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፤ በዱባይ መካሄድ ጀምሯል። ዶክተር ፍጹም ይሄንን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ እንደገለጹት በስፍራው ኢትዮጵያ ያዘጋጀችው ኤግዚቢሽን በአረንጓዴ አሻራ ያስመዘገበችውን ስኬትና ሌሎችንም ተሞክሮዎች ለዓለም ማህበረሰብ ለማስተዋወቅ መልካም አጋጣሚ ይፈጥራል። ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ልማት ስራዋን በአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ላይ በተዘጋጀው የኢትዮጵያ አውደ ርእይ/ፓቪሊዮን/ በማስተዋወቅ ላይ መሆኗንም ገልጸዋል። በ1ሺህ 500 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ትልቅ ኢግዚብሽን በማዘጋጀት ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ በተጨባጭ ለውጥ እያመጣች መሆኗን የምናሳይበት ነው ብለዋል። በጉባኤውም መሪዎች ንግግር በማድረግ ከዚህ ጋር በተያያዘ የሚዘጋጁ ስብሰባዎች ላይ በመሳተፍ በአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ ዙሪያ ድምጿን ታሰማለች ብለዋል። በዚህም በዘርፉ የተከናወኑ ስራዎችን በማስተዋወቅ ብሎም እያጋጠሙ በሚገኙ ተግዳሮቶች ዙሪያ የአፍሪካ ድምጽ በመሆን ትልቅ ተሳትፎ ይኖረናል ሲሉም ገልጸዋል። በዚህ ኤግዚቢሽንም በተለያዩ ዞኖች ማለትም የኢትዮጵያን አረንጓዴ አሻራ ኢንሼቲቭ እና ያስገኘውን ጥቅሞች በተመለከተ ለዕይታ ይቀርባል ብለዋል። በተጨማሪም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በማጉላት ዘላቂ የግብርና ልማት ተሳትፎዎች ላይ በማተኮር በስንዴ ልማት እምርታዊ ለውጥ የታየበት ነውም ብለዋል።
የፌዴራል ድጎማ በጀት ቀመር ለማሻሻል በሚያስችሉ የቅድመ ዝግጀት ሥራዎች ላይ ውይይት ተካሄደ
Nov 30, 2023 40
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ)፦በበቂ መረጃ የተደገፉ ስራዎችን ማከናወን ለፌዴራል ድጎማ በጀት ቀመር ማሻሻል ሂደት ቁልፍ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች መሆናቸው ተገለጸ፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት የድጎማ የጋራ ገቢዎች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴና ጉዳዩ የሚመለከታቸው የፌዴራል ተቋማት ከፍተኛ ሃላፊዎች የፌደራል ድጎማ በጀት ቀመር ለማሻሻል በሚያስችሉ የቅድመ ዝግጀት ሥራዎች ላይ ውይይት አካሂደዋል፡፡ በመድረኩ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አባላትና የክልል ርዕሳነ መስተዳደሮችን ጨምሮ ከገንዘብ ሚኒስቴር፣ ከፕላንና ልማት ሚኒስቴር፣ ከገቢዎች ሚኒስቴር፣ ከኢትዮጵያ ስታስቲክስ አገልግሎት ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት የክልሎችና የፌዴራል መንግሥት የጋራ ተብለው የተመደቡ ገቢዎች በሁለቱ መካከል የሚከፋፈሉበትን፤ እንዲሁም የፌዴራሉ መንግሥት ለክልሎች ድጎማ የሚሰጥበትን ቀመር የመወሰን፤ ከሀገራዊ ኃላፊነቶቹ መካከል በዋናነት የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ ምክር ቤቱም የተጣሉበትን ኃላፊነቶችና የወጡ ሕጎችን ተከትሎ የሕገ መንግሥት የበላይነት፣ ሕገ መንግስታዊነት፣ ዘላቂ ሰላም፣ ዴሞክራሲ ለማረጋገጥ፣ እንዲሁም አንድ የፖለቲካና ኢኮኖሚ ማህበረሰብ ለመገንባት ሀገራዊ ሃላፊነቱን ለመወጣት የበኩሉን ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል በክልሎች መካከል ውጤታማና ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍልን ለማረጋገጥ የሚረዳ የፌዴራል ድጎማና የጋራ ገቢዎች ቀመር እንዲዘጋጅ በማድረግ፤ የማከፋፈያ ቀመሮቹ በፍትሃዊ የሀብት ክፍፍልና በክልሎች የተመጣጠነ እድገት ላይ ያላቸዉን አንድምታ እንዲጠና በማድረግ ሰፊ ስራዎች ሲሰራ መቆየቱን አንስቷል፡፡ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር አሁን ያለው ቀመርና አፈጻጸሙ እንደገና መፈተሽ አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ከቋሚ ኮሚቴውና ከሚመለከታቸው የፌደራል ባለድርሻ አካለት ጋር ግብዓት ለመሰብሰብ የታለመ መድረክ ነው ብለዋል፡፡ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ የፊስካል ፌዴራሊዝም ሪፎርም መደረጉንና በርካታ ውጤቶች የተገኙበት መሆኑን አስታውሰዋል፡፡ በቀጣይም የኢትዮጵያ ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄዎችን በተገቢው የሕግ አግባብ ለመመለስ ቁርጠኝነት እንደሚፈልግና ለዚህም ሁሉም ባለ ድርሻ አከላት በርብርብና በእኔነት ስሜት ሊሰራ እንደሚገባም ነው ያሳሰቡት፡፡ በቀጣይ ለሚደረገው የቀመር ማሻሻል ስራ ከሚደረግ ቅድመ ዝግጅት ጋር ተያይዞ በጥናትና በበቂ መረጃ የተደገፉ ስራዎችን መስራት ለቀመር ማሻሻል ሂደት ቁልፍ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች መሆናቸውንም አስገንዝበዋል፡፡ በመደረኩ የሚነሱ አስተያየቶችና ሀሳቦች ቋሚ ኮሚቴው ለሚያዘጋጀውና ለምክር ቤት ለሚቀርበው ሀገራዊ ሰነድ ትልቅ ግብዓት ሆኖ እንደሚወሰድም ነው የገለጹት፡፡ ለቀመር ዝግጅት የሚያስፈልጉ መረጃዎች ወቅታዊና ተአማኒነት ያላቸው እንዲሆኑ በቂ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ማከናወን እንደሚገባ የጋራ ስምምነት መደረሱን ተጠቅሷል። በመረጃ አቅርቦት ረገድ ሃላፊነት የተጣለባቸው የፌዴራልና የክልል ተቋማት ትኩረት ሰጥተው እንዲሰሩ አቅጣጫ መቀመጡን የፌዴሬሽን ምክር ቤት መረጃ ያመላክታል፡፡
በአዲስ አበባ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አገልግሎቶች ሙሉ በሙሉ በኦን ላይን ሆነዋል
Nov 30, 2023 41
አዲስ አበባ፤ ህዳር 20/2016(ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አገልግሎቶች ሙሉ በሙሉ በኦን ላይን መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ንግድ ቢሮ አስታወቀ፡፡ በአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ የ2016 በጀት ዓመት የመጀመሪያው ሩብ አመት ዕቅድ አፈጻጸሙን ከባለድርሻ አካላት ጋር ዛሬ ገምግሟል፡፡ የቢሮው ምክትል ሃላፊ መስፍን አሰፋ፤ በሩብ አመቱ አገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን፣ የፍጆታ ምርት አቅርቦትን በማሳለጥና ህገ ወጥ ንግድን በመከላከል በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል፡፡ የቢሮውን አገልግሎት አሰጣጥ ዘመናዊ በማድረግና ለደንበኞች እርካታ ለመፍጠር የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አገልግሎት ሙሉ በሙሉ በኦን ላይን እንዲሰጥ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አገልግሎት አሰጣጥ በኦን ላይን መሆኑም የደንበኞችን እንግልትና ተጨማሪ ወጪ ያስቀረ መሆኑን ገልጸዋል። የምርት አቅርቦትና ፍላጎት አለመጣጣምን ተከትሎ የሚከሰተውን የኑሮ ውድነት ለመቆጣጠር ነባር የእሁድ ገበያዎችን የማስፋት ተግባር መከናወኑን ገልፀዋል፡፡ አሁን ላይ የእሁድ ገበያ ማዕከላት ቁጥር 172 መድረሱን የገለጹት ምክትል ሃላፊው በተሰራው ስራ ህብረተሰቡ ጥራት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ ማስቻሉን ገልጸል፡፡ የግብርና ምርቶች እጥረት እንዳያጋጥም በአምስቱ የመዲናዋ መግቢያ በሮች ዘመናዊ የግብርና ምርቶች ማዕከላት እንዲገነቡ መደረጉን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም በለሚ ኩራ፣ ኮልፌና አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተሞች የተገነቡት ዘመናዊ የገበያ ማዕከላት ግንባታቸው ተጠናቀው ስራ መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ በሌላ በኩል በተደረገ የክትትልና የቁጥጥር ስራ ከ10 ሺህ በላይ ህገ ወጥ ነጋዴዎች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን ጠቁመዋል፡፡
ኢትዮጵያ የዓለም የሥራ ድርጅት አባል የሆነችበትን 100ኛ ዓመት በማስመልከት ሀገር አቀፍ ጉባኤ ሊካሄድ ነው
Nov 30, 2023 55
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዓለም የሥራ ድርጅት (ILO) አባል የሆነችበትን 100ኛ ዓመት በማስመልከት ሀገር አቀፍ ጉባዔ ሊካሄድ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስትሯ ሙፈሪሃት ካሚል የጉባኤውን መካሄድ በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል። ጉባኤው "ማህበራዊ ምክክርን እና የጎለበተ ምርታማነትን በመጠቀም ማህበራዊ ፍትህን ማላቅ" በሚል መሪ ሃሳብ ከኅዳር 24 እስከ 26 ቀን 2016 ዓ.ም በተለያዩ ኩነቶች ይካሄዳል ብለዋል። በጉባዔው ባለድርሻ አካላት በጋራ ሆነው ስኬቶች የሚገመገሙበት፣ ልምዶች የሚቀመሩበት ለዘርፉ መጠናከር የሚያግዙ ምክረ ሀሳቦች የሚንሸራሸሩበት ይሆናል ብለዋል። የዓለም ሥራ ድርጅት ሲቋቋም ኢትዮጵያ ከአፍሪካ በቀዳሚነት አባል መሆኗን አስታውሰው ይህም ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የትብብር መድረኮች ላይ ሁሌም ግንባር ቀደም ሚና እንደምትጫወት ማሳያ ነው ሲሉም ተናግረዋል። በመስኩ ሥራቸውን በአግባቡ በመከወን ውጤታማ መሆን የቻሉ አካላትና ሠራተኞች ዕውቅና የሚሰጥበት መርሃ ግብር መዘጋጀቱንም አስታውቀዋል። በጉባዔው ከዓለም የሥራ ድርጅት ጋር ያለውን ትብብር እና ስኬቶች፣ የገጠሙ ተግዳሮቶች የሚፈታበት አቅጣጫ ላይ የጋራ ሀሳብ የሚያዝበት መሆኑንም ገልጸዋል።
520 ሺህ ኩንታል ዩሪያ ማዳበሪያ የጫነች መርከብ ጅቡቲ ወደብ ደርሳለች-የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ
Nov 30, 2023 44
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ) ፦ 520 ሺህ ኩንታል ዩሪያ የአፈር ማዳበሪያ የጫነች መርከብ ጅቡቲ ወደብ መድረሷን የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አስታወቀ። ተጨማሪ 615 ሺህ ኩንታል ኤን ፒ ኤስ ቦሮን የጫነች መርከብ ነገ ህዳር 21 ቀን 2016 ዓ.ም ጅቡቲ ወደብ እንደምትደርስ ይጠበቃል ብሏል። በዚህም እስከአሁን 2 ሚሊዮን 84 ሺህ 685.1 ኩንታል ዩሪያ መጓጓዙን ከኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ የተገኘው መረጃ ያመላክታል። ይህ በእንዲህ እንዳለ እስክ ታህሳስ 3 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ ተጨማሪ 1 ሚሊዮን 130 ሺህ ኩንታል ኤን ፒ ኤስ ቦሮን ወደብ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስታውቋል። የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን (ኢግሥኮ) ለ2016/17 የምርት ዘመን ከውጭ ከገዛው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ እስከ ዛሬ ህዳር 20 ቀን 2016 ዓ.ም ድረስ በአምስት ዙሮች 2 ሚሊዮን 84 ሺህ 685.1 ኩንታል ዩሪያ መጓጓዙንም ጨምሮ ገልጿል። ከዚህ ውስጥም 1 ሚሊዮን 92 ሺህ 178 ኩንታል ዩሪያ ከጂቡቲ ወደብ ወደ ሀገር ውስጥ ተጓጉዞ ለአርሶ አደር ዩኒየኖች እየተሰራጨ መሆኑን ጠቁሟል። የኢትዮጵያ የባሕር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ የአፈር ማዳበሪያን በባሕር እና በየብስ የማጓጓዙን ሂደት በስኬት እያከናወነ መሆኑን ገልጾ የድርጅቱ ከፍተኛ አመራሮች ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የማጓጓዙ ሂደት ውጤታማ በሆነ መልኩ እንዲከናወን ያለሰለሰ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉም ብሏል።
የኢትዮጵያ ልማት ባንክ የግብርና ዘርፉን በስፋት ለመደገፍ የሚያስችል የወለድ ተመን ማሻሻያ አደረገ
Nov 30, 2023 58
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ የግብርና ዘርፉን በስፋት ለመደገፍ የሚያስችል የወለድ ተመን ማሻሻያ ማድረጉን አስታወቀ። ባንኩ በግብርና ዘርፍ በአነስተኛ፣ መካከለኛና የኮርፖሬት ፕሮጀክት ብድር 11 ነጥብ 5 በመቶ የማበደሪያ የወለድ ተመን ወደ 7 በመቶ ዝቅ አድርጓል። በማሻሻያው በሊዝ ፋይናንስና በፕሮጀክት ፋይናንስ የብድር ሞዳሊቲ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶችን ማካተቱም ተመላክቷል። ባንኩ ዛሬ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳመላከተው ከምስረታው ጀምሮ ለግብርና ዘርፉ ትኩረት በመስጠት ሲደግፍ የቆየ የፖሊሲ ባንክ መሆኑን በመጥቀስ ግብርናውን ለማሻሻል መንግስት እየወሰደ ያለውን እርምጃ ማሳካት እንዲቻልና የግብርና ሴክተሩን በማነቃቃት በዘርፉ የግል ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት እና ለመሳብ የባንኩ የሥራ አመራር ቦርድ የወለድ ተመን ማሻሻያ ማድረጉን አሳውቋል፡፡ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ባለፉት ዓመታት ባካሄደው ሪፎርም የነበሩበትን ተግዳሮቶች እየቀረፈና አዳዲስ አገልግሎቶችን ለደንበኞች እያቀረበ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎችን እየሰራ እንደሚገኝ በመግለጫው የተመላከተ ሲሆን ይህ የወለድ ተመን ማሻሻያም ወቅቱን የጠበቀ እና በአገራችን ያለውን ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ማዕከል ያደረገ መሆኑን አብራርቷል፡፡ ባንኩ የወለድ ተመን ማሻሻያ ማድረጉን አስመልክቶ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ዮሐንስ አያሌው እንዳሉት፣ “የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ኢትዮጵያ ያላትን ከፍተኛ የሆነ ያልታረሰ የመሬት ሀብት ወደ ስራ ለማስገባት፤ ባለሀብቶች፣ አርሶ አደሮች እና አርብቶ አደሮች የበለጠ እንዲበረታቱ ለማድረግ በግብርና ዘርፍ በአነስተኛ፣ መካከለኛና የኮርፖሬት ፕሮጀክት ብድር ለሚጠይቁ ይጠበቅ የነበረው የ11.5 በመቶ የማበደሪያ የወለድ ተመን ወደ 7 በመቶ ዝቅ አድርጓል።” ባንኩ ስራ ላይ ያዋለው ይህ ማሻሻያ ዘርፉን ለማሳደግ ያቀደው ስትራቴጅያዊ ሪፎርም አካል ሲሆን፣ መንግስት የግብርና ዘርፉን ለማሳደግ እየሰራ ያለውን ስራ የበለጠ የሚያግዝ መሆኑንም ገልፀዋል። ባንኩ የወለድ ተመን ማሻሻያ ማድረጉ በአምራች ዘርፉ የተሰማሩ ድርጅቶች በጥሬ እቃ አቅርቦት እጥረት ምክንያት የነበረባቸውን ዝቅተኛ የማምረት አቅም በማሻሻልና በውጭ ምንዛሬ የሚገቡ ምርቶችን ለመቀነስ ከመርዳቱም በላይ ሀገራችን በዘርፉ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ የሚያግዝ መሆኑም ተብራርቷል። በተጨማሪም የተደረገው የወለድ ተመን ማሻሻያ የምግብና የኢንዱስትሪ ሰብሎች ላይ ያተኮረ ሥራ በኢንቨስተሩ እንዲሰራ የሚያበረታታ ሲሆን፣ የምግብ ፍላጎትንና ለኢንዱስትሪ የሚሆኑ የጥሬ ዕቃዎች አቅርቦት ሙሉ በሙሉ በአገር ውስጥ ምርቶች ከማሟላት ጎን ለጎን፣ የምግብ ዋጋ ንረትን ለማረጋጋትና የውጭ ምንዛሬ አቅምን ለማሳደግ እንደ መንግስት እየተሰራ ያለውን ስራ እንደሚያጠናክር ይጠበቃል። ለከፍተኛ፣ ለአነስተኛና መካከለኛ የግብርና ፕሮጀክቶች የተደረገው የማበደሪያ ወለድ ምጣኔ ማሻሻያ ባንኩ ለዘርፉ ዕድገት ያለውን ቁርጠኛ አቋም ያሳየበት መሆኑም በመግለጫው ተመላክቷል። በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ የሀገራችንን ኢኮኖሚያዊ ልማት በተሻለ ደረጃ እንዲረጋገጥ አሁን በገበያው ውስጥ ካለው ነባራዊ ሁኔታ በመነሳት በተመረጡ ዘርፎች ለተሰማሩ እና ግዙፍ ፕሮጀክቶችን ለሚያንቀሳቅሱ ተበዳሪዎች በሌሎች አገልግሎቶች ላይ መጠነኛ የወለድ ተመን ማሻሻያ ማድረጉ ተጠቁሟል።
በኢትዮጵያ ለመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ወጥነት ያለው የአሰራር መስፈርትና የህግ ማዕቀፍ ሊዘጋጅ ነው
Nov 30, 2023 38
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ)፦ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር በሀገሪቱ የመስኖ ልማት ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍ ያለመ ወጥነት ያለው የአሰራር መስፈርትና የህግ ማዕቀፍ ለማዘጋጀት የአንድ ዓመት ፕሮጀክት ይፋ አደረገ። ከዓለም የምግብና እርሻ ድርጅት በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ የሚተገበረው ይህ ፕሮጀክት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እንደሚከናወን ተገልጿል። የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትሯ ኢንጅነር አይሻ መሀመድ በዚህ ወቅት እንዳሉት በመስኖ መሰረተ ልማት ግንባታዎች ጥናት፣ ዲዛይንና ጥገና ረገድ አሁንም ተግዳሮቶች አሉ። ለአብነትም በቴክኖሎጂ አጠቃቀም፣ የአቅም ውስንነት፣ የሕግ ማዕቀፍ፣ የጥራት እንዲሁም በተያዘላቸው ጊዜ ገደብና በጀት አለመጠናቀቅ ከሚስተዋሉ ችግሮች ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል። ወጥ አሰራር እና መመሪያ ባለመኖሩ 75 በመቶ የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች በዲዛይን ጥራት ችግር እንደሚጓተቱ ጠቁመዋል። ይህን ችግር በዘላቂነት ለመቅረፍም የሀገሪቷን ነባራዊ ሁኔታ እና ተፈጥሯዊ ሀብት ያገናዘበ የመስኖ ልማትን ለመደገፍ ወጥነት ያለው የአሰራር መስፈርት፣ መመሪያና የህግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት እንዳስፈለገ ገልጸዋል። ይህን እውን የሚያደርግና በአንድ ዓመት የሚጠናቀቅ ፕሮጀክት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ዛሬ ይፋ መደረጉን ጠቁመዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ዶክተር ሳሙኤል ክፍሌ፣ ዩኒቨርሲቲው ፕሮጀክቱን በተያዘለት ጊዜ አጠናቆ ለማስረከብ ሃላፊነቱን በአግባቡ እንደሚወጣ ገልጸዋል። በቀጣይም በሀገራዊ የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ዙሪያ የሚያደርገውን ሙያዊ ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው ያመላከቱት።
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ለህዳሴ ግድብ ግንባታ የሚውል ከ44 ሚሊዮን ብር በላይ ቦንድ ሽያጭ ተከናወነ
Nov 30, 2023 38
ጭሮ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ)፦በምዕራብ ሐረርጌ ባለፉት ሁለት ወራት ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የሚውል ከ44 ሚሊዮን ብር በላይ ቦንድ ሽያጭ መከናወኑን የዞኑ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ፈሪድ ይስሃቅ ለኢዜአ እንደገለጹት ቦንዱን የገዙት የዞኑ መንግሥት ሠራተኞች፣ አርሶ አደሮች፣ ነጋዴዎችና ባለሀብቶች ናቸው። በዞኑ በወራቱ ለመሸጥ የታቀደው 40 ሚሊዮን ብር ቦንድ ቢሆንም፣ ሕዝቡ ባደረገው የተሻለ ተሳትፎ ክንውኑ የአራት ሚሊዮን ብር በብልጫ መመዝገቡን አስታውቀዋል፡፡ የዞኑ ሕዝብ በግል እስከ 200 ሺህ ብር ድረስ ዋጋ ያለው ቦንድ በመግዛት ያደረገው ተሳትፎ የሚያስደስትና ይበል የሚያሰኝ መሆኑንም ሃላፊው ገልጸዋል፡፡ በቦንድ ግዥው ከተሳተፉ የዞኑ ነዋሪዎች መካከል የመንግሥት ሠራተኛዋ ወይዘሮ ወሲላ መዬ በአንድ ወር ደሞዛቸው ቦንድ በመግዛት ሀገራዊ ግዴታቸውን መወጣታቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም "የ500 ብር ቦንድ በመግዛት የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ አስተዋጽኦ በማድረጌ ደስታ ተሰምቶኛል" ብለዋል፡፡ የመንግሥት ሠራተኞችና ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች ለህዳሴው ግድብ ግንባታ የሚያደርጉትን ድጋፍ እንዲያጠናክሩም ጠይቀዋል ወይዘሮ ወሲላ፡፡ የሒርና ቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ኮሌጅ ዲን አቶ ሽመልስ ታከለ በበኩላቸው ተቋሙ ሰሞኑን ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ የሚውል የ15 ሺህ ብር ቦንድ መግዛቱን ተናግረዋል፡፡ የኮሌጁ ማህበረሰብ የግድቡ ግንባታ ፍጻሜ እስኪያገኝ ድረስ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል፡፡ ከዞኑ ባለፈው በጀት ዓመት ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡን ከጽህፈት ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የሕዳሴውን ግድብ ከዳር ለማድረስ ቦንድ መግዛታችንን እንቀጥላለን--የጅማ ባለሀብቶች
Nov 30, 2023 43
ጅማ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ)፦የታላቁ ኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ከዳር ለማድረስ በቦንድ ግዢ የሚያደርጉትን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩ የጅማ ከተማ ባለሀብቶች ገለጹ። በከተማዋ በትናንትናው ዕለት ብቻ ለግድቡ ግንባታ የ20 ሚሊዮን ብር ቦንድ ሽያጭ ተከናውኗል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ያነጋገራቸው ቦንድ የገዙ ባለሀብቶች እንደተናገሩት በኢትዮጵያውያን የጋራ ትብብር የተጀመረው ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክት በትብብር ለማስፈፀም ተሳትፏቸውን ያጠናክራሉ። ግድቡ ኢትዮጵያዊያንን በአንድነት ያስተሳሰረ፣ የኅብረታችን ውጤትና የአንድነታችን ማሳያ መሆኑንም ተናግረዋል። ከባለሀብቶቹ መካከል የ600 ሺህ ብር ቦንድ የገዙት ወይዘሮ ሮዛ ቢያ ''ሀገራችንን ለማሳደግና የተሻለ የኑሮ ደረጃ እንዲኖረን በሀገር ልማት መሰተፍ ያስፈልጋል'' ብለዋል። በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን፣ የሀገር ውስጥ ባለሀብቶች እንዲሁም ህብረተሰቡ የሕዳሴውን ግድብ በኅብረት እንደጀመርነው ሁሉ በኅብረት ማጠናቀቅ አለብን ብለዋል። "ግድቡ ለሀገሪቱ በቂ ኤሌክትሪክ በማመንጨት በሕዝቡ ሕይወት ላይ ትርጉም ያለው ለውጥ ለማምጣት ያስችላል ብዬ አምናለሁ'' ሲሉም ባለሀብቷ ተናግረዋል። ሌላኛው ባለሀብት አቶ በድሩ ሰማን በበኩላቸው የሀገሪቱ ብሩህ ተስፋ የሆነውን ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ከፍጻሜ ለማድረስ የድርሻቸውን እየተወጡ መሆናቸውን አስታውቀዋል። በዚህኛው ዙር የ300 ሺህ ብር ቦንድ በመግዛት ድጋፍ ማድረጋቸውንና በቀጣይም ተሳትፏቸውን እንደሚያጠናክሩ አረጋግጠዋል። የኤሌክትሪክ ሃይል ልማትና አገራዊ ዕድገትን ለማፋጠን ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ባለሀብቱ፤ ዜጎች የግድቡን ግንባታ ለማጠናቀቅ ርብርብ ማድረግ አለብን ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። "የሀገር ተስፋ ለሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ቦንድ በመግዛት ድጋፍ ማድረግ ይኖርብናል" ያሉት ደግሞ የ50 ሺህ ብር ቦንድ የገዙት ሌላዋ ባለሀብት ወይዘሮ አሚና አባነጋ ናችው። እሳቸውም ከዚህ በፊት ቦንድ በመግዛት የዜግነት `ሃላፊነታቸውን ሲወጡ መቆየታቸውን ገልጸው፣ ለወደፊትም ተጨማሪ ቦንድ በመግዛት ተሳትፎ እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል። መላው ኢትዮጵያውያን በአንድነትና በትብብር የጀመርነውን የግድቡን ግንባታ እስከ ፍጻሜው ማድረስ ይጠብቅናል በማለትም አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለማህበረሰብ ጤና መድህን አገልግሎት ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ እየደጎመ ነው
Nov 30, 2023 26
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ ለማህበረሰብ ጤና መድህን አገልግሎት በየአመቱ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ እየተደጎመ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ጤና ቢሮ ገለጸ፡፡ የማኅበረሰብ አቀፍ የጤና መድን ኢንሹራንስ በሀገር አቀፍ ደረጃ መተግበር ከጀመረ 11 ዓመት አስቆጥሯል። የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ ባለፉት አራት ዓመታት በመዲናዋ የሚገኙ ሁሉንም ወረዳዎችን በማካተት የማኅበረሰብ አቀፍ የጤና መድን አገልግሎትን ተደራሽ ማድረግ ችሏል። የቢሮው ኃላፊ ዶክተር ዮሐንስ ጫላ፤ በመዲናዋ የማኅበረሰብ አቀፍ የጤና መድን አገልግሎት እየሰፋ መምጣቱን ገልጸዋል። በመዲናዋ ከጥቅምት 1 ጀምሮ እስከ ህዳር 30 ቀን 2016 ዓ.ም የማኅበረሰብ ጤና መድን አገልግሎት ነባር እና አዲስ አባላት ምዝገባ እየተካሄደ ይገኛል ብለዋል። በአነስተኛ ገቢ ለሚተዳደሩ ከ86 ሺህ በላይ አባወራ /እማወራ ሥር የሚገኙ 350 ሺህ ነዋሪዎችን ሙሉ ወጪ መሸፈኑን ተናግረዋል። የከተማ አስተዳደሩ ለእያንዳንዱ ግለሰብ የአባልነት ክፍያ 500 ብር በመደጎም በየዓመቱ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ እየደጎመ መሆኑን ገልጸዋል። ቢሮው የማኅበረሰብ አቀፍ ጤና መድን ኢንሹራንስ መመዝገብ የሚችል የማኅበረሰብ ክፍል ሳይመዘገብ እንዳይቀር እየሰራ መሆኑንም ዶክተር ዮሐንስ ተናግረዋል። በማኅበረሰብ አቀፍ የጤና መድን ኢንሹራንስ በአባልነት የተመዘገበ በየትኛውም የመንግሥት ጤና ተቋም አገልግሎት ማግኘት እንደሚችልም ጠቁመዋል። የማኅበረሰብ አቀፍ ጤና መድህን የአባልነት እድሳት ለማከናወን ምንም አይነት ክፍያ የማይጠየቁ ቢሆንም በዓመት አንድ ሺህ ብር መዋጮ የመክፈል ግን ግደታ አለባቸው። በዚህ ዓመት ተጨማሪ 200 ሺህ አባላትን እየተሰራ ሲሆን ከኅዳር 30 በኋላ ለመመዝገብ የሚመጡ ነባርም ሆነ አዲስ አባላትን ማስተናገድ አይቻልም ተብሏል።
በምዕራብ ወለጋ 66 ሺሕ ሄክታር መሬት በመስኖ ስንዴ ልማት በዘር ተሸፍኗል
Nov 30, 2023 34
ግምቢ ፤ኅዳር 20/2016 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ወለጋ ዞን 66ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ በዞኑ በበጋ የመስኖ ስንዴ ልማቱ ከ94ሺህ በላይ አርሶ አደሮች የተሳተፉ ሲሆን፣ ከሦስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅም ተገልጿል። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ፈይሳ ሐምቢሳ እንዳስረዱት በዞኑ እየተካሄደ ባለው የዘንድሮው በጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከ92ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ይለማል። ልማቱን በተቀናጀ መልኩ ለማከናወን የተለያዩ ግብዓቶች ለአርሶ አደሩ እየቀረቡ መሆናቸውንም አክለዋል፡፡ በዚህም በኩታ ገጠምና በሌሎች የግብርና ቴክኖሎጂ ተደግፎ በሚካሄደው ልማት እስካሁን 65ሺህ 987 መሬት በዘር መሸፈኑን አስታውቀዋል፡፡ በልማቱ 39ሺህ 963 ኩንታል ማዳበሪያና 539 ኩንታል ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ መዋሉንም አክለዋል፡፡ በዚህ ዓመት በሚካሄደው የበጋ መስኖ የስንዴ ልማት 94ሺህ 456 አርሶ አደሮች እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸው፣ ከልማቱም ከሦስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ እየተለመደ በመጣው በበጋ የመስኖ ስንዴ ልማት በርካታ አርሶ አደሮች እየተሳተፉና የምርት ዓይነታቸውን እያሰፉ መሆናቸውንም በመልካም ጎኑ አንስተዋል። በልማቱ እየተሳተፉ ካሉ አርሶ አደሮች መካከል የላሎ አሳቢ ወረዳ ነዋሪው አቶ ሙላቱ ታደሰ እንዳሉት የበጋ መስኖ ስንዴ ከተጀመረ ወዲህ የአርሶ አደሩን ኑሮ ከማሻሻል ባለፈ የምግብ ዋስትናቸውን እያረጋገጡበት ነው። ዘንድሮም በባለሙያ ምክርና በግብርና ቴክኖሎጂ ታግዘው ሩብ ሄክታር መሬታቸውን በስንዴ ዘር መሸፈናቸውን ገልጸዋል፡፡ የግምቢ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ዓለሙ መገርሳ በበኩላቸው በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ በግማሽ ሄክታር መሬታቸው ላይ ስንዴ እያለሙ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ በኢትዮጵያ በበጋ ወቅት የመስኖ ልማት ማካሄድ ባለፉት ጥቂት ዓመታት እየተለመደ የመጣ ሲሆን፣ በዚህ ወቅት ከሚለሙት መካከል ስንዴ ግንባር ቀደም ሰብል ሆኖ መምጣቱን መረጃዎች ያመለክታሉ።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በበጋ መስኖ 146 ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ዝግጅት እየተደረገ ነው
Nov 30, 2023 38
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ) ፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የደረሱ ስብሎችን ከመሰብስብ ጎን ለጎን በበጋ መስኖ 146 ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። የኢዜአ ሪፖርተር በማዕከላዊ ኢትዮጰያ ክልል የግብርና እንቅስቃሴን በሚመለከት በተለይም በሀላባ፣ ስልጤ እና ሌሎችም አካባቢዎች የመስክ ምልከታ አድርጓል። በመስክ ምልከታውም አርሶ አደሮቹ የደረሱ ሰብሎችን ከመሰብሰብ ጎን ለጎን ለበጋ መስኖ ልማት ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን አረጋግጧል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የጽህፈት ቤት ኃላፊ አህመድ ሀቢብ፤ በክልሉ በበልግ እና በመኸር እርሻ 491 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች መልማቱን ገልጸዋል። ከልማቱም ከቅመማ ቅመም በርበሬና ሮዝመሪ ከ41 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት የሚሰበሰብ መሆኑን ጠቅሰዋል። አሁን ላይ በ 177 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተዘራና የደረሰ ሰብል የተሰበሰበ ሲሆን ከዚህም ከ8 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ማግኘት ተችሏል ብለዋል። ከ150 በላይ ኮምባይነሮችን ለምርት ስብሰባ መዘጋጀት መሰብሰብ ላይ መሆኑን ጠቁመዋል። በክልሉ የደረሱ ሰብሎችን ከመሰብሰብ ጎን ለጎን ለበጋ መስኖ ልማት እየተደረገ ባለው 146 ሺህ ሄክታር መሬት የሚለማ መሆኑንም ገልጸዋል። በስልጤ እና ሃላባ ዞኖች ካነጋገርናቸው አርሶ አደሮች መካከል አህመድ ውሃረብ እና አብዱሰላም ከድር የደረሱ ሰብሎችን በኮምባይነር ጭምር እየሰበሰቡ መሆኑን ተናግረዋል። በኮምባይነር ምርቱን መሰብሰብ መቻሉ ለፍጥነትና የምርት ብክነትን በማስቀረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገላቸው መሆኑን ገልጸዋል።፡ በስልጤ ዞን የምስራቅ ስልጤ ወረዳ አርሶ አደሮች፤ ለበጋ የመስኖ ልማት የምርጥ ዘር እና የግብአት አቅርቦት መሟላቱን ጠቅሰው ዘንድሮ ካለፈው ዓመት የተሻለ ምርት ለማግኘት ዝግጅት አድርገናል ብለዋል።
ማዕከሉ በሐረሪ ክልል ለአካባቢው ስነ ምህዳር ምቹና ውጤታማ የሆኑ የሰብልና የአትክልት ምርጥ ዝርያዎችን እያስፋፋ ነው
Nov 30, 2023 103
ሐረር፤ህዳር 20/2016 (ኢዜአ) ፦የፈዲስ ግብርና ምርምር ማዕከል በሐረሪ ክልል ለአካባቢው ስነ-ምህዳር ምቹና ውጤታማ የሆኑ የሰብልና የአትክልት ምርጥ ዝርያዎችን እያስፋፋ መሆኑን አስታወቀ። በምርምር ማዕከሉ የግብርና ኤክስቴንሽን ቡድን መሪ አቶ አብዱላዚዝ ጠሀ ለኢዜአ እንደገለጹት ማዕከሉ ምርትና ምርታማነትን ለማጎልበት በድሬዳዋ አስተዳደር፣ በሐረሪ ክልልና በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ቴክኖሎጂን የማስተዋወቅ፣ የማላመድና የማስፋፋት ሥራ እያከናወነ ይገኛል። በአሁኑ ወቅትም በሐረሪ ክልል ከአካባቢው የአየር ፀባይ እና መልከዓ-ምድራዊ አቀማመጥ ጋር ተስማሚ የሆኑ የሰብል፣ የአትክልትና የእንስሳት መኖ ምርጥ ዘሮችን እያስፋፋ መሆኑን ጠቁመዋል። በማዕከሉ ተላምደው በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ እየተስፋፉ ያሉ የሰሊጥ፣ የቲማቲም፣ የበቆሎ እና የተለያዩ እንስሳት መኖ ምርጥ ዘሮች መሆናቸውን አስረድተዋል። በተለይ ከባኮ ግብርና ምርምር ተገኝተው በማዕከሉ ተላምዶ እየተስፋፋ ያለው “ሃጫሉ” የተባለው የሰሊጥ ዝርያ በክልሉ ኤረር ወረዳ በሄክታር እስከ 7 ኩንታል ምርት መስጠቱ በተግባር መረጋገጡን አቶ አብዱላዚዝ ተናግረዋል። "መልካሳ አራት እና መልካ ሾላ" የተባሉት የበቆሎና የቲማቲም ምርጥ ዝርያዎችም የዝናብ እጥረትና በሽታን ተቋቁመው ምርት የሚሰጡ መሆናቸውን ነው ያስረዱት። በአርሶ አደሩም ተቀባይነት በማግኘታቸው እየተስፋፉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ዝርያዎቹ በተለይ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ መረጋጋት ፋይዳቸው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። ማዕከሉ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማጎልበት በክልሉ ኤረር ወረዳ ዶዶታ ቀበሌ ገበሬ ማህበር የሰብል፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርጥ ዝርያዎችን ከአርሶ አደሩ ጋር የማስፋፋት ሥራ እያከናወነ ይገኛል ያሉት ደግሞ የሐረሪ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ነስረዲን አህመድ ናቸው። እንደእሳቸው ገለጻ ማዕከሉ በክልሉ የሚያከናውነው የግብርና ቴክኖሎጂን የማስፋፋት ሥራ አርሶ አደሩ በዓመት አንዴ ከማምረት ተላቆ ሦስትና አራት ጊዜ እንዲያመርት የሚያስችል ነው። ቴክኖሎጂው በክልሉ በግብርና ምርቶች ላይ እየተስተዋለ ያለውን የዋጋ ንረት ለማረጋጋት የራሱ አበርክቶ እንዳለውም ገልጸዋል። እንደ አቶ ነስረዲን ገለጻ በዘንድሮ በጋ ወራት በክልሉ ከ4ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመስኖ ለማልማት ዝግጅት ተጠናቋል። በሐረሪ ክልል ግብርና ቢሮ የእርሻ ልማት ባለሙያ አቶ አክሊሉ ሽፈራው በበኩላቸው፣ የምርምር ማዕከሉ ለአርሶ አደሩ የሚያስፋፋው የሰብልና የአትክልት ዝርያዎች በሽታን ተቋቁመው በአጭር ጊዜ የሚደርሱ መሆናቸው በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በተግባር ታይቷል። በማዕከሉ እየተስፋፋ የሚገኘው የሰብልና የአትክልት ምርጥ ዘር ዝርያዎች አርሶ አደሩ ምርቶቹን በብዛትም በጥራትም ማምረት እንዲችል እገዛ እያደረገ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። በኤረር ወረዳ የኤረር ዶዶታ ቀበሌ ገበሬ ማህበር አርሶ አደር እድሪስ ዩሱፍ እንደገለጹት የፈዲስ ግብርና ምርምር ማዕከል የሚያቀርብላቸውን ምርጥ ዘር በመጠቀም ቴክኖሎጂን የማስፋፋት ሥራ እያከናወኑ ይገኛሉ። የሰብልና የአትክልት ምርጥ ዝርያዎቹ በሽታን ተቋቁመው የተሻለ ምርት የሚሰጡ መሆኑንና ይህንንም በእርሻ ሥራቸው ለማረጋገጥ እንደቻሉ ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅት ቴክኖሎጂውን ለሌሎች የማስፋፋት ሥራ እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። ከማዕከሉ የተሰጣቸውን “ሃጫሉ” የተባለ የሰሊጥ ምርጥ ዘር በመውሰድ እያመረቱ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ አርሶ አደር መሀመድ ጠሃ ናቸው። "ምርጥ ዘሩ በአጭር ጊዜ የሚደርስ መሆኑን በተግባር በመመልከቴ ደስተኛ ነኝ፤ ማዕከሉንም ለማመስገን እፈልጋለሁ" ሲሉም ገልጸዋል።
ሁለንተናዊ የልማት ትስስርና ማህበራዊ ቁርኝትን ለማሳደግ የመንገድ መሰረት ልማትን ማሳለጥ እንደሚገባ ተገለጸ
Nov 30, 2023 42
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ) ፦በኢትዮጵያ ሁለንተናዊ የልማት ትስስርና ማህበራዊ ቁርኝትን ለማሳደግ የመንገድ መሰረት ልማትን ማሳለጥ እንደሚገባ የተለያዩ ክልሎች የስራ ሃላፊዎች ገለጹ። በኢትዮጵያ በተለይም በመንገድ መሰረተ ልማት እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶችን ሀገራዊ ፋይዳ እና የህብረተሰብ ጠቀሜታ በማስመልከት ኢዜአ የተለያዩ ክልሎች የስራ ሃላፊዎችን አነጋግሯል። ከአስተያየት ሰጭዎቹ መካከል የአማራ ክልል መንገድ ቢሮ ሃላፊ ዶክተር ጋሻው አወቀ፤ በተለያዩ አካባቢዎች እየተከናወኑ ያሉ የመንገድ መሰረተ ልማቶች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የገጠር መንገዶችን ከዋና መንገዶች ጋር በማገናኘት እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ከኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸው ባለፈ የዜጎችን ማህበራዊ መስተጋብር በማጠናከር በኩል ሚናቸው የጎላ ነው ብለዋል። የህዝብ ቅሬታና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ከሚነሱባቸው ጉዳዮች መካከል አንዱ የመንገድ መሰረተ ልማት መሆኑን ጠቅሰው አሁን የተጀመሩ ስራዎች ለሀገር ልማትና ማህበራዊ ቁርኝት ወሳኝ መሆናቸውን ጠቅስዋል። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ሃላፊ ፋጂዮ ሳፒ፤ የብሄር ብሄረሰቦችን ትስስር የበለጠ ለማጠናከር የመንገድ መሰረተ ልማቶች ትልቅ ትርጉም አላቸው ብለዋል። በመሆኑም ለሀገር ልማት ዘላቂ ሰላምና የህዝቦችን አብሮነት ለማጠናከር በህብረተሰብ ተሳትፎ የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን አጠናክረን እንቀጥላለን ነው ያሉት። የጋምቤላ ክልል መንገድ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ቢተው ዳክ፤ በመንገድ መሰረተ ልማት የተሳሰሩ አካባቢዎች ላይ ያለው የህዝቦች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስተጋብር ይበለጥ እየተጠናከረ መምጣቱን ገልጸዋል። የመንገድ መሰረተ ልማት በተለይም ለግብርና ልማትና ምርታማነት፣ ለማዕድን ልማት እንዲሁም የግብርና ግብዓቶችን በቀላሉ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ የላቀ አበርክቶ ያለው መሆኑ ይታወቃል። በኢትዮጵያ ያለውን ብዝሃነት ሁለንተናዊ ትስስርና ማህበራዊ ቁርኝት በማጠናከር ለአገር ልማትና ዕድገት ለመጠቀም የተጀመሩ ጥረቶችን እንቀጥላለን ሲሉ ሃላፊዎቹ አረጋግጠዋል። በመሆኑም የገጠር መንገድ ተደራሽነትን በማስፋት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ፕሮጀክት የከተማና መሠረተ-ልማት ሚኒስቴር በቅርቡ ይፋ ማድረጉ ይታወቃል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን በህዳር ወር ከ400 ኩንታል በላይ እጣንና ሙጫ ተሰበሰበ
Nov 30, 2023 48
መተማ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ) ፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን በያዝነው ዓመት ከ9 ሺህ 400 ኩንታል በላይ የእጣንና ሙጫ ምርት ለማምረት ትኩረት መሰጠቱን የዞኑ የደንና ዱር እንስሳት ተጠሪ ጽ/ቤት አስታወቀ። በዞኑ በእጣንና ሙጫ ከተሸፈነው ከ234 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ከ49 ሺህ ኩንታል በላይ የማምረት እምቅ አቅም አለ። በጽህፈት ቤቱ የአካባቢ ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ሀብታሙ አድጎ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ ከ9 ሺህ 400 ኩንታል በላይ የእጣንና ሙጫ ምርት ለማምረት ታቅዶ በያዝነው የህዳር ወር ብቻ ከ400 ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ተችሏል። በዞኑ የሚመረተውን የእጣንና ሙጫ ምርት ወደ ገበያ አቅርቦ በመሸጥ ከ291 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ በማግኘት አምራቾችን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የማምረት ሂደቱን ለማሳለጥም 15 ባለሃብቶች፣ 21 ማህበራት፣ አራት ኢንተርፕራይዞችና አንድ ተቋም እውቅና ተሰጥቷቸው ስራ መጀመራቸውን አብራርተዋል። በእጣንና ሙጫ ማምረት ተግባሩም ከሶስት ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የስራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እንደሚሰራም ተናግረዋል። የቴዎድሮስ የተፈጥሮ ሀብት ልማት ግብይት ማህበራት ዩኒየን ስራ አስኪያጅ አቶ ክንዱ ወርቁ እንደተናገሩት፤ ዩኒየኑ ባለፈው ዓመት ከ3 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለሽያጭ አቅርቦ ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ አግኝቷል። በያዝነው ዓመትም በስሩ የሚገኙ 18 ማህበራትን በማሰማራት ከ4 ሺህ 300 ኩንታል በላይ እጣን አምርቶ ለገበያ በማቅረብ ካለፈው ዓመት የተሻለ ገቢ ለማግኘት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በቋራ ወረዳ በአዲስ ልደት ቀበሌ የዘላቂ ተፈጥሮ ሀብት ህብረት ስራ ማህበር ሰብሳቢ አቶ ደሴ አባይ እንዳሉት፤ በዚህ ዓመት ከ500 ኩንታል በላይ እጣን ለማምረት ተዘጋጅተዋል። ባለፈው ዓመት ከ400 ኩንታል በላይ እጣንና ሙጫ በማምረት 12 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ ማግኘታቸውን ጠቁመው ዘንድሮ ጥራት ያለው ምርት በማቅረብ የተሻለ ገቢ ለማግኘት እየሰሩ ነው። በምዕራብ ጎንደር ዞን ከ234 ሺህ ሄክታር በላይ በእጣንና ሙጫ ከተሸፈነው መሬት በዓመት ከ49 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት የማምረት አቅም ቢኖርም ለሥራው ትኩረት ካለመስጠትና በወቅታዊ ችግር ሳቢያ የታሰበውን ያህል ለማምረት አልተቻለም። በዞኑ ባለፈው በጀት ዓመት ከተመረተው ከ9 ሺህ 200 ኩንታል በላይ እጣንና ሙጫ ምርት ከ151 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ከዞኑ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በሲዳማ ክልል ህብረተሰብን ያሳተፈ የሙስና መከላከል ተግባር ውጤት እያስገኘ ነው - ኮሚሽኑ
Nov 29, 2023 61
ሀዋሳ ፤ ህዳር 19 /2016 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል እየተካሄደ ባለው ህብረተሰብን ያሳተፈ የሙስና መከላከል ተግባር ውጤት እያስገኘ መምጣቱን የክልሉ የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ። የክልሉ የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽነር ወይዘሮ ዘላለም ለማ ዛሬ ማምሻውን በሰጡት መግለጫ እንዳመለከቱት፤ በክልሉ ህብረተሰብን በማሳተፍ እየተካሄደ ባለው የፀረ ሙስና ትግል ውጤት እየተመዘገበበት ነው። ህብረተሰቡ የሚስተዋሉ የሙስናና ብልሹ አሰራሮችን የመጠቆምና አጋልጦ የመስጠት ልምዱ እየዳበረ መምጣቱን ጠቁመው፤ ይህም በክልል ደረጃ መልካም የሚባሉ ውጤቶች እንዲመዘገቡ ማድረጉን ገልጸዋል። ይህን ለማጠናከር እየተሰራ ነው ያሉት ኮሚሽነሯ፣ የህዝብን ንቃተ ህሊና ይበልጥ ለማጎልበትና ተሳትፎን ለማሳደግ ዓመታዊ የፀረ ሙስና ቀንን በተለያዩ ዝግጅቶች ማክበር ጠቀሜታ እንዳለው ጠቅሰዋል። የዘንድሮው የፀረ - ሙስና ቀን "ሙስና የጋራ ጠላታችን ነው!" በሚል መሪ ሀሳብ በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ መሆኑን አመልክተው፤ በህዝባዊ ንቅናቄው ከቀበሌ እስከ ክልል ድረስ የሙስና ትግልን የሚያጠናክሩ ሥራዎች እንደሚሰሩ ተናግረዋል። ሙስና የልማት ሥራዎችን የሚያደናቅፍና ሰላምን የሚያውክ መሆኑን ያመለከቱት ኮሚሽነር ወይዘሮ ዘላለም፤ በፀረ ሙስና ትግሉ የህዝቡን ተሳትፎ ማጽናት እንደሚያስፈልግም አስታውቀዋል። ህብረተሰቡ በየአካባቢው የሚመለከተውን የሙስናን ችግር በግልጽ በማንሳትና ጥቆማ በመስጠት ለፀረ ሙስና ትግሉ የጀመረውን አጋርነት እንዲያጠናክርም ኮሚሽነሯ አሳስበዋል። በክልሉ ከተቋቋመው የፀረ ሙስና ግበረ ኃይል ጋር በመቀናጀት ባለፈው ዓመት በተደረገ እንቅስቃሴ ውጤት መገኘቱንም አመልክተዋል። ባለፈው ዓመት ለክልሉ ግብረ ኃይል ከህዝቡ 218 ጥቆማ መድረሱን ያስታወሱት ኮሚሽነሯ፤ ጥቆማውን መሠረት በማድረግ በተወሰደው አስቸኳይ ሙስናን የመከላከል እንቅስቃሴ ከ110 ሚሊዮን ብር በላይ የህዝብና የመንግሥት ሀብት ማዳን እንደተቻለም አስታውቀዋል። በተጨማሪም በህገ ወጥ መንገድ ሊተላለፍ የነበረ 59 ሺህ ሄክታር የገጠር መሬት ወደ መሬት ባንክ ማስመለስ መቻሉን ተናግረዋል። በማዳበሪያ ስወራና በሌሎች የሙስና ወንጀሎች የተጠረጠሩ 505 ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው በ256 የክስ መዝገቦች በፍርድ ሂደት ላይ መሆኑን ጠቁመው፣ ከመካከላቸው የፍርድ ውሳኔ የተሰጣቸው እንዳሉም አብራርተዋል። ኮሚሽነር ዘላለም እንዳሉት፤ በክልሉ 99 በመቶ የሚሆኑ የህዝብ ተመራጮች፣ ተሿሚዎች፣ የመንግስት ሠራተኞች፣ የልማት ድርጅቶች እና የህዝባዊ ድርጅቶች የሥራ ኃላፊዎችና ሠራተኞች ሃብታቸውን እንዲያስመዘግቡ ተደርጓል። በመንግስት መስሪያ ቤቶች፣ የልማት ድርጅቶች እና በህዝባዊ ድርጅቶች ውሰጥ ለሙስናና ብልሹ አሰራር የተጋለጡ እና ሊጋለጡ የሚችሉ የአሰራር ስርዓቶችን እንዲጠኑ እንደሚደረግ ጠቅሰው፤ ኮሚሽኑ የሙስና ተጋላጭነት ችግርን ለመከላከል አበክሮ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ለሙስና ተጋላጭ በሆኑ ተቋማት በተለዩ ችግሮች ላይ ምክረ ሀሳብ በመስጠት የተቋማት አመራር አባላት ችግሮችን እንዲያርሙና እንዲያስተካክሉ የመፍትሄ ሃሳብ እንደሚሰጣቸው የገለጹት ኮሚሽነሯ፣ ይህንን ተግባራዊ በማያደርጉት ላይ እርምጃ ለመውሰድ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ክልላዊ የዘንድሮ የጸረ ሙስና ቀን ማጠቃለያ መርሀ ግብር ህዳር 21 ቀን 2016 ዓም በይርጋለም ከተማ እንደሚካሄድ ታውቋል።
ለብሔራዊ ባንክ የሚቀርበው የወርቅ ምርት እንዲጨምር በህገወጦች ላይ ጠንካራ እርምጃ እየተወሰደ ነው-የባንኩ ገዥ ማሞ ምህረቱ
Nov 29, 2023 93
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 19/2016(ኢዜአ):- ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የሚቀርበው የወርቅ ምርት እንዲጨምር በህገወጦች ላይ ጠንካራ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን የባንኩ ገዥ ማሞ ምህረቱ ገለጹ። ለህጋዊ አምራቾች ማበረታቻ በመስጠት ለባንኩ የሚቀርበው የወርቅ ምርት እንዲጨምር እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክና ተጠሪ ተቋማት በ2016 በጀት የባንክ የሩብ ዓመት አፈጻጸም ላይ ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ጋር ውይይት አድርገዋል። የባንኩ ገዥ ማሞ ምህረቱ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ ወርቅ ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ ነው። ከጥቂት ዓመታት በፊት ወርቅ ወደ ውጪ በመላክ እስከ 600 ሚሊዮን ዶላር ይገኝ እንደነበር አስታውሰው፤ በህገወጥ ንግድና በተለያዩ ችግሮች ገቢው እያሽቆለቆለ መጥቷል ብለዋል። በተለይም ወርቅ አምራች በሆኑ አካባቢዎች የጸጥታ ችግር እንዲፈጠርና ሃብቱ በህገወጥ መንገድ እንዲወጣ በማድረግ አንዳንድ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች ጭምር እጃቸው እንዳለበት ነው ያነሱት። በመሆኑም ወደ ብሔራዊ ባንክ የሚቀርበው የወርቅ ምርት እንዲጨምር የክልል መንግስታት ጠንካራ ድጋፍ ሊያደርጉ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። አክለውም ባንኩ ከጸጥታና ደህንነት ተቋማት ጋር በመቀናጀት ህገወጥ የወርቅ ምርትና ግብይትን ለመቆጣጠር እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህም ጠንካራ እርምጃ እየተወሰደ ነው ብለዋል። ማዕድናት በአግባቡ ተመርተው ለውጭ ገበያ እንዲቀርቡ የባለድርሻዎች የትብብር መድረክ መቋቋሙን ያነሱት የብሔራዊ ባንክ ገዥ፤ ለወርቅ አምራቾች እስከ 70 በመቶ ማበረታቻ በመስጠት የተሻለ ውጤት እየተገኘ መሆኑን ጠቅሰዋል። የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጆ በበኩላቸው፤ ብሔራዊ ባንክ የወርቅ ምርት በበቂ ሁኔታ ለማዕከላዊ ገበያ እንዲቀርብ ተጨማሪ መመሪያና ፖሊሲ ማውጣት አለበት ብለዋል። ህገ-ወጥ የወርቅ ግብይትን ለመከላከልም ሌሎች ባለድርሻዎች ባንኩን ማገዝ እንዳለባቸው በመጠቆም። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የጥቁር ገበያ የውጭ ምንዛሬ መከላከል ላይ በልዩ ትኩረት ሊሰራ እንደሚገባም በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳስቧል።
ኢትዮጵያ ከፓኪስታን ጋር ያላት የንግድ ግንኙነት ጠንካራና ሚዛኑን የጠበቀ እንዲሆን ትኩረት ማድረግ ይገባል-ቋሚ ኮሚቴው
Nov 29, 2023 68
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 19/2016(ኢዜአ):- ኢትዮጵያ ከፓኪስታን ጋር ያላት የንግድ ግንኙነት ጠንካራና ሚዛኑን የጠበቀ እንዲሆን በልዩ ትኩረትና በቅንጅት መስራት እንደሚገባ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የንግድና ቱሪዝም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አስታወቀ። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ገብረ መስቀል ጫላ በበኩላቸው የኢትዮጵያንና የፓኪስታንን የንግድ ግንኙነት የሚያሳልጥ የጋራ ኮሚቴ በማቋቋም የአሰራር ሰርዓት መዘርጋቱን ተናግረዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የንግድና ቱሪዝም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኢትዮጵያና ፓኪስታን መካከል በተፈረመው የሁለትዮሽ የንግድ ሥምምነት ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር ተወያይቷል። በረቂቅ አዋጁ ላይ ከፓርላማ አባላትና ባለድርሻ አካላት ጥያቄዎች ቀርበው በሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል። የንግድ ሥምምነቱ በጥናት ላይ ተመስርቶ ስለመፈረሙ፣ ኢትዮጵያን የተሻለ ተጠቃሚ የሚያደርግ ስለመሆኑ፣ በአገራቱ መካከል ያለውን የንግድ ሚዛን ለማጣጣም ይዞት ስለመጣው ፋይዳ በውይይቱ ላይ ተነስቷል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ገብረመስቀል ጫላ በሰጡት ማብራሪያ፤ በአገራቱ መካከል የተፈረመው ሥምምነት ጥናት ላይ የተመሰረተ፤ የአገራቱን ተጠቃሚነት ከግምት ያስገባ መሆኑን ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያና ፓኪስታን መካከል ያለው ግንኙነት እየተጠናከረ መምጣቱን የጠቆሙት ሚኒስትሩ በኢኮኖሚ ዲፕሎማሲው መስክም የበለጠ ለመተሳሰር ሥምምነቱ ፋይዳው የጎላ ነው ብለዋል። ስምምነቱ አገራቱ የንግድ ትርኢቶችን በማካሄድ፣ የልምድ ልውውጦች በማድረግ በኢኮኖሚው መስክ ግንኙነቱ የበለጠ እንዲጠናከር አጋዥ መሆኑንም አስረድተዋል። እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ በአገራቱ መካከል በሚካሄደው የንግድ ግንኙነት ዙሪያ የሚገጥሙ ችግሮችን ለመፍታት ከሁለቱ አገራት የተውጣጣ የጋራ ኮሚቴ የተቋቋመ ሲሆን ኮሚቴው በየጊዜው እየተገናኘ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን የሚያስቀምጥበት አሰራር ተዘርግቷል። ሚኒስትሩ እንዳሉት፤ ሥምምነቱ በኢትዮጵያና በፓኪስታን መካከል የሚኖረውን የንግድ ግንኙነት ሚዛኑን ለማስጠበቅ ትልቅ ጠቀሜታ አለው። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዓለም አቀፍ ሕግ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ረታ ዓለሙ በበኩላቸው ሥምምነቱ ዓለም አቀፍ የንግድ ሥርዓቱን የጠበቀ መሆኑን አብራርተዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የንግድና ቱሪዝም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ አሻ ያህያ በበኩላቸው ሥምምነቱ የሁለቱን አገራት ግንኙነት የሚያሳልጥ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ከፓኪስታን ጋር ያላት የንግድ ግንኙነት ጠንካራና ሚዛኑን የጠበቀ እንዲሆን የዘርፉ የመንግስት ተቋማትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በልዩ ትኩረትና በቅንጅት መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል። ቋሚ ኮሚቴው በሥምምነት ረቂቅ አዋጁ ላይ አስፈላጊውን ግብዓት ማሰባሰቡን ጠቁመው ረቂቅ አዋጁ በቅርቡ እንደሚፀድቅ ጠቁመዋል።
በቤንች ሸኮ ዞን በሙስና ሊመዘበር የነበረ ከ5 ሚሊዮን ብር በላይ ተመላሽ ተደረገ
Nov 29, 2023 59
ሚዛን አማን ፤ ህዳር 19 /2016 (ኢዜአ)፡- በቤንች ሸኮ ዞን በሙስና ወንጀል ሊመዘበር የነበረ ከ5 ሚሊዮን ብር በላይ ተመላሽ መደረጉን የዞኑ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት መምሪያ አስታወቀ። "ሙስና የጋራ ጠላታችን ነው በኅብረት እንታገል" በሚል መሪ ሳብ የጸረ ሙስና ቀን ዛሬ በሚዛን አማን ከተማ ተከብሯል። በዚህ ወቅት የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሳሙኤል አሰፋ እንዳሉት ፤ ሙስናን መከላከል ላይ በተከናወነው ስራ የሌብነት ድርጊቶች እየተጋለጡ ነው። በዚህም በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያዎቹ ሶሰት ወራት በሙስና ሊመዘበር የነበረ ከ5 ሚሊዮን ብር በላይ ወደ መንግስት ካዝና ማስመለስ መቻሉን አስታውቀዋል። ገንዘቡ ሊመዘበር የነበረው በተለያዩ መስሪያ ቤቶች ባልተገባ አበል፣ በቼክ ማበላለጥና በሌሎችም ማጭበርበሮች መሆኑን አስረድተዋል። በተያያዘም ከህጋዊ አሰራር ወጪ የሆነ 19 ሚሊዮን ብር በኦዲት ግኝት መለየቱን ጠቅሰው፤ የመንግስት ፋይናንስ የአሠራር ሥርዓትን በተከተለ መልኩ ለማስመለስ እየሰራን ነው ብለዋል ። ከማጭበርበርና ብክነት ጋር ተያይዞ የተጠረጠሩ ከ30 በላይ ግለሰቦችን በህግ ተጠያቂ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አቶ ሳሙኤል አስታውቀዋል። ህብረተሰቡም ሙስናና ሌሎችንም ህገወጥ ድርጊቶችን በመጠቆምና በማጋለጥ የድርሻውን እንዲወጣም መልዕክት አስተላልፈዋል። በቤንች ሸኮ ዞን አስተዳደር የሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና ሥራ ሂደት አስተባባሪ አቶ ኤልያስ ሽባብ፤ ሙስና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የሥነ ምግባር ግንባታ ተግባር ሌብነትን ለመከላከል እንደሚረዳ ገልጸው ፤ከትምህርት ቤት ጀምሮ የተለያዩ ስልጠናዎችን እየሰጠን ነው ብለዋል። ለህዝብ መሠረት ልማት ግንባታ መዋል የሚገባው ገንዘብ እንዳይባክን ጥቆማ የመቀበል ሥርዓቱን በማስፋት በህግ የማስጠየቁ ሥራ እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። በጸረ ሙስና ቀን በዓል ላይ ከታደሙት መካከል አቶ ምትኩ በየነ በሰጡት አስተያየት፤ ሙስና የሀገር ኢኮኖሚን የሚያቀጭጭ አስጸያፊ ድርጊት በመሆኑ ሁላችንም ልንታገል ይገባል ብለዋል። ብልሹ አሰራሮችን ከሁሉም የመንግስት መሥሪያ ቤቶች ለይቶ ለማስተካከል በቁርጠኝነት መሰራት እንዳለበት ጠቁመዋል። ሌላዋ ተሳታፊ ወይዘሮ ተስፋነሽ ኢያሱ ፤ ሙስና የሚያስከትለው ችግር በመገንዘብ የመከላከሉ ተግባር የሁሉም ሀላፊነት መሆኑን ተናግረዋል። የጸረ ሙስና ተቋማትን የአሠራር ሥርዓት ማጠናከርና በገለልተኝነት እንዲንቀሳቀሱ ማስቻል እንዲሁም ጥቆማ የሚሰጡ አካላትን ደኅንነት እንዲጠበቅ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመዋል። በሚዛን አማን ከተማ በዞን ደረጃ በተከበረው የፀረ ሙስና ቀን ላይ የዞን ተቋማት የመንግስት አመራር አባላትና ሰራተኞች ተሳትፈዋል።
የኤሌክትሮኒክስ የመንግስት ግዥ የአሰራር ሥርዓት ብክነትን በማስወገድ ፍትሃዊነት እንዲረጋገጥ ያደርጋል
Nov 29, 2023 133
ሀዋሳ፤ህዳር 19/2016 (ኢዜአ)፡- ፍትሃዊና ለብክነት ያልተጋለጠ የግዥ አሰራርን ለመዘርጋት የኤሌክትሮኒክስ የግዥ ሥርዓት በሁሉም ደረጃ ባሉ የመንግስት ተቋማት እንዲተገበር እየተሰራ መሆኑን የመንግስት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ገለፀ ፡፡ የሲዳማ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ከመንግስት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ጋር በመተባበር በኤሌክትሮኒክስ የመንግስት ግዥ የአሰራር ሥርዓት ላይ ለአቅራቢዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ሰጥቷል ፡፡ በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የመንግስት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃጂ ኢብሳ የኤሌክትሮኒክስ የመንግስት ግዥ ከሌሎች ሀገራት ልምድ በመውሰድ በኢትዮጵያ ከ2014 ዓ.ም ጀምሮ ገቢራዊ የሆነ የግዥ ሥርዓት እንደሆነ ተናግረዋል ፡፡ የአሰራር ሥርዓቱ በተለይ በመንግስት ግዥዎች ላይ ፍትሐዊነትን በማረጋገጥ ለብክነት ያልተጋለጠ ሂደትን በማስፈን ረገድ የጎላ ሚና እንዳለው ተናግረው በሁሉም ደረጃ ባሉ የመንግስት ተቋማት ላይ ተግባራዊ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል ፡፡ በ2014 ዓ.ም ትግበራው ሲጀመር በዘጠኝ የፌዴራል ተቋማት ላይ መሆኑን አውስተው አሁን ላይ 169 የፌዴራል ተቋማት ወደ አሰራር ሥርዓቱ ገብተዋል ብለዋል ፡፡ በክልሎች ደግሞ ለመጀመሪያ ጊዜ በሲዳማ ክልል በተመረጡ ዘጠኝ ተቋማት ወደ ሥርዓቱ እንዲገቡ በሙከራ ደረጃ መጀመሩን ጠቅሰዋል ፡፡ በፌዴራል ደረጃ እስካሁን ከ38 ሺህ ባለይ የሚሆኑ የንግዱ ማህበረሰብ አባላት በዚህ አሰራር ዙሪያ ሥልጠና እንደተሰጣቸውም ጠቁመዋል ፡፡ የንግዱ ማህበረሰብ በዚህ የአሰራር ሥርዓት የመንግስት ጨረታዎችን በተመለከተ በቀላሉ መረጃ ከማግኘት ባሻገር የሚወዳደሩትም በኤሌክትሮኒክስ ሥርዓት በመሆኑ ጊዜና ወጪያቸውን በከፍተኛ ደረጃ እንደሚቀንስላቸው አስረድተዋል ፡፡ ሥርዓቱ መንግስት በግዥ ሂደት ውስጥ የሚፈፀምን ሌብነትና አድሏዊ አሰራሮችን በመከላከል ፍትሐዊነትና ግልፀኝነትን ማረጋገጥ የሚያስችለው አሰራር እንደሆነ ጠቁመዋል ፡፡ ''ፍትሃዊነት በገንዘብ የማይተመን ነው'' ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ከወጪ አኳያ ባለው ዓለም አቀፍ ተሞክሮ በዚህ የአሰራር ሥርዓት ሀገራት ከ5 እስከ 25 በመቶ ዓመታዊ በጀታቸውን መቆጠብ እንደቻሉም አብራርተዋል ፡፡ የሲዳማ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ ዶክተር አራርሶ ገረመው በክልሉ ለጅማሮ ዘጠኝ ክልላዊ ተቋማት ወደዚህ ሥርዓት እንደሚገቡ ገልፀዋል ፡፡ በቀጣይ በሁሉም ደረጃ ያሉ የመንግስት ተቋማት ወደ ሥርዓቱ እንደሚገቡም ጠቁመዋል ፡፡ ከዓመታዊ የክልሉ በጀት ከ60 በመቶ በላይ የሚውለው ለግዥ ነው ያሉት ኃላፊው ይህን ያህል ሀብት የሚዘዋወርባቸው የመንግስት ግዥዎች ከአድሎና ኢፍትሐዊ አሰራር ነፃ እንዲሆኑ ማድረግ ለሁሉም አካላት አስተዋፅኦው ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ በፊት የመንግስት ግዥ ጨረታዎች ሲወጡ ረጅም ጊዜን እንዲሁም የወረቀትና ሌሎች ወጪዎችን እንደሚጠይቁ አስታውሰው ይህንን የሚያስቀር አሰራር ነው ብለዋል ፡፡ በሥልጠናው ከተሳተፉ የንግዱ ማህበረሰብ አባላት መካከል በግንባታ ተቋራጭነት ዘርፍ ላይ የተሰማሩት አቶ ጎበዛየሁ ፋንታ "የኤሌክትሮኒክስ ግዥ ዘመናዊ የጨረታ ሥርዓት እንዲኖር በማድረግ ሥራዎቻችንን ቀላል የሚያደርግ ነው" ብለዋል ፡፡ ወጪያችንን በመቆጠብና ከአድሎ ነፃ የሆነ ውድድር እንዲኖር መደላድልን በመፍጠር ረገድ ጠቀሜታው ከፍተኛ በመሆኑ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተባብረን በመስራት የሚጠበቅብንን እንወጣለን ብለዋል ፡፡ በስልጠናው ላይ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች የተገኙ ሲሆን ከ260 በላይ የሚሆኑ አቅራቢዎች ተሳትፈዋል፡፡