ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በምስራቅ ሸዋ ዞን ከበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከ11ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቧል 
Apr 15, 2026 38
አዳማ፤ ሚያዚያ 7/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን ከዘንድሮው የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት እስካሁን ድረስ ከ11 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጽህፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በ2018 የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት 250 ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ 301 ሺህ 160 ሄክታር በማልማት ከዕቅድ በላይ ለማሳካት ተችሏል። የበጋ መስኖ ስንዴ ልማቱ የከርሰ ምድር ውሃ እና የአዋሽ ወንዝን በመጥለፍ የተካሄደ መሆኑንም ጠቁመዋል።   የውሃ አማራጮቹን በመጠቀም በዞኑ 11 ወረዳዎች ከለማው መሬት ውስጥ እስካሁን ከ50ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የደረሰ የስንዴ ሰብል በሰው ጉልበት ታጭዶ መሰብሰቡን ጠቁመዋል። ከ208 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የለማው የበጋ መስኖ ስንዴም በኮምባይነር ታግዞ መሰብሰቡን ነው የገለጹት። የምርት አሰባሰቡን ለማቀላጠፍና የምርት ብክነትን ለመከላከል እንዲቻል 125 ኮምባይነሮች በዞኑ እንዲሰማሩ መደረጉንም አመላክተዋል። በእጅና በኮምባይነር ታግዞ በተደረገ የምርት አሰባሰብ ሂደት እስካሁን ድረስ ከ11 ሚሊዮን 104 ሺህ ኩንታል በላይ የስንዴ ምርት መሰብሰቡን አቶ አብነት ተናግረዋል።   እንደ እሳቸው ገለፃ በዞኑ በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከተሸፈነው አጠቃላይ መሬት ከ13 ሚሊዮን 100 ሺህ ኩንታል ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ በቅድመ ምርት ትንበያ ወቅት ተገምቷል። አብዛኛው መሬት በኩታ ገጠም እና በሜካናይዜሽን እርሻ የለማ ሲሆን ይህም ምርትን በፍጥነት ለመሰብሰብና ምርታማነትን ለማሳደግ የጎላ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አውስተዋል። የመስኖ ልማት ሥራው በዞኑ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር የአርሶ አደሩን ገቢ በማሳደግ ምጣኔ ሀብታዊ ተጠቃሚቱን እያሳደገውም ብለዋል።   በዞኑ እስካሁን በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከ285 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በመሳተፍ ተጠቃሚ መሆናቸውንም አብራርተዋል። በመስኖ ልማት ዘንድሮ በምርታማነት ብልጫ እንዳለ የገለጹት አቶ አብነት፣ ለዚህም ወደ ልማት ያልገቡ ቀበሌዎች በነፍስ ወከፍ የውሃ ጉድጓድ በመቆፈር ጭምር ወደ ልማት መግባታቸውን በምክንያትነት ጠቅስዋል።
የኢኮኖሚ ሪፎርሙ በሀገር በቀል እውቀት የተቃኘ እና በራስ ባለቤትነት የሚመራ ነው- እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)
Apr 15, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ እየተተገበረ የሚገኘው የኢኮኖሚ ሪፎርም በሀገር በቀል እውቀት የተቃኘ እና በራስ ባለቤትነት የሚመራ መሆኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ። የ2026 የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) እና የዓለም ባንክ የፀደይ ወቅት ስብሰባ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ይገኛል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ከስብሰባው ጎን ለጎን በተዘጋጀ የልማት አቅም ግንባታ መድረክ ላይ ተሳትፈዋል። እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ የኢትዮጵያን አጠቃላይ የፋይናንስ ዘርፍ ማሻሻያ አጀንዳ ለከፍተኛ የዓለም አቀፍ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች አብራርተዋል። በስብሰባው ላይ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት ፣ ከዓለም ባንክ እና ከአውሮፓ ኮሚሽን የተወከሉ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል። የባንኩ ገዥ "ገበያዎችን፣ተቋማትን እና መረጋጋትን በፈታኝ ወቅቶች ውስጥ መገንባት" በሚል መሪ ርዕስ በሰጡት ገለጻ፤ በኢትዮጵያ የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ አማካኝነት በፋይናንስ ሥርዓቱ ላይ እየተከናወነ ያለውን መዋቅራዊ ሽግግር በዝርዝር አቅርበዋል። በዚህም ዘርፉን ለማዘመን እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎችን ለተሳታፊዎች አስረድተዋል።   የባንኩ ገዥ ኢትዮጵያ ወደ ወለድ ተመን ተኮር የገንዘብ ፖሊሲ ማዕቀፍ እያደረገች ያለውን ሽግግር እና በገበያ የሚወሰን የውጭ ምንዛሬ ተመን ሥርዓት ትግበራን በዋናነት አንስተዋል። በተጨማሪም በአዲሱ የብሔራዊ ባንክ አዋጅ እና በዘመናዊ የባንክ ሥራ ሕግጋት የታገዘው የቁጥጥር ማዕቀፍ፣ የሀገሪቱን የፋይናንስ መዋቅር ሙሉ በሙሉ እየለወጠው እንደሚገኝ ገልጸዋል። የገዢው መልዕክት ዋነኛ ማጠንጠኛም የሪፎርም ባለቤትነት ሲሆን፤ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች በሀገር በቀል እውቀት የተቃኙ እና በስትራቴጂያዊ ቅደም ተከተል የሚመሩ መሆናቸውን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። ከተለያዩ አካላት የሚገኘው ማንኛውም የቴክኒክ ድጋፍም ቢሆን በሀገሪቱ ፍላጎት ላይ የተመሠረተና ከልማት የቅድሚያ ትኩረቶች ጋር የተጣጣመ እንጂ ከውጭ ተጽዕኖ የሚመነጭ አለመሆኑን አስገንዝበዋል። ወደፊት ስለሚከናወኑ ተግባራት ማብራሪያ የሰጡት የባንክ ገዥው፤ በቀጣዩ ምዕራፍ የሀገር ውስጥ የፋይናንስ ገበያን ይበልጥ ማሳደግ እና ዘርፉን ለውጭ ኢንቨስትመንት ክፍት ማድረግ የሪፎርሙ ቀዳሚ አጀንዳዎች መሆናቸውን አመልክተዋል። ለዚህም ዘላቂ ለውጥ ለማምጣት ተከታታይነት ያለው የተቋማት አቅም ግንባታ፣ የፖሊሲ ቀጣይነት እና የግል ዘርፉን የሚመራውን ኢኮኖሚ መሸከም የሚችል ጠንካራ የፋይናንስ ሥርዓት መገንባት ወሳኝ መሆኑን መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
የክልሉ መንግስት የሕዝቡን ሕይወት የሚቀይሩ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ ነው- ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ
Apr 15, 2026 56
ቢሾፍቱ፤ ሚያዚያ 7 /2018 (ኢዜአ)፦ የኦሮሚያ ክልል መንግስት ግልጽ ዕቅድ በማስቀመጥ የሕዝቡን ሕይወት የሚቀይሩ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ ተናገሩ። የኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት እና የፓርቲ የሦስተኛ ሩብ ዓመት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ በቢሾፍቱ ከተማ መካሄድ ጀምሯል። በግምገማ መድረኩ ላይ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ እና የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ሰዓዳ አብዱራህማን፣ በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ እና ሌሎች የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት፤ ባለፉት ዓመታት የክልሉ መንግስት ግልጽ ዕቅድ በማስቀመጥ የሕዝቡን ሕይወት የሚቀይሩ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ ነው ብለዋል። በተለይም በሁሉም ዘርፎች በኢኒሼቲቭ መልክ ሲተገበሩ የቆዩ የልማት ስራዎች በክልሉ መሰረታዊ ለውጦች እንዲመዘገቡ ያስቻሉ መሆናቸውን አንስተዋል።   በመድረኩ ላይ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተከናወኑ የመንግስት እና የፓርቲ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርቶች ቀርበው፣ የታዩ ጥንካሬዎችና ድክመቶች ተለይተው ለቀጣይ ሥራዎች አቅጣጫ ይቀመጣልም ተብሏል። በተጨማሪም የ2019 ዓ.ም የዕቅድ መነሻ የሚቀርብ ሲሆን፣ በግምገማው ላይ የዞን፣ የከተማ እና የወረዳ አመራሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
የከተማ እና ከተሜነት እሳቤ ለሀገር ግንባታ መሰረት ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 15, 2026 215
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ የከተማ እና ከተሜነት እሳቤ ለሀገር ግንባታ ቁልፍ ሚና እንዳለው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። “የሉዓላዊነት ልብ” በሚል ርዕሰ ጉዳይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ጋር ቆይታ አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቆይታቸው የከተማ እና የከተሜነት እሳቤ ለሀገረ መንግስት ግንባታ ስኬት ያለውን ወሳኝ ሚና አስመልክተው ገለጻ አድርገዋል። በገለጻቸውም የሀገረ መንግስት ግንባታ ሊከናወንና ሊሳካ የሚችለው በጥግግት የሚኖሩ ሰዎች ሲኖሩ መሆኑን አስገንዝበዋል። በጥግግት የሚኖር ማህበረሰብ ለኢኖቬሽን እና ለውድድር እጅግ ወሳኝ መሆኑንም አብራርተዋል። የሕዝብ ጥግግት ለልማት እጅግ ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ልማትንና ብልጽግናን የሚያስብ ማንኛውም መንግስት ከተማን፣ ከተሜነትን፣ ግብር መክፈልንና አገልግሎት መስጠትን ማዕከሉ ካላደረገ ልማት ሊያመጣ እንደማይችል አስገንዝበዋል። ከተማ አያስፈልግኝም፣ የእኔ ትኩረት አርሶ አደር ብቻ ነው የሚል እሳቤ ካለ ልማትን ማሰብ እንደማይቻልም አክለው ገልጸዋል። በጥግግት የሚኖር ማህበረሰብ የመፍጠር አቅሙ ከፍተኛና የነቃ መሆኑን ገልጸው ማህበረሰቡ ግብር የሚከፍልና ለመሠረተ ልማት ቅርብ በመሆኑ የሚነገረውን በቅርበት እንደሚሰማም አስረድተዋል። መንግስት ከትናንትናው ጠቃሚ የሆኑ ጉዳዮችን በመውሰድ ቀጣይነትን ማረጋገጥ ላይ ትኩረት ማድረጉን ገልጸዋል። ባለፉት ጊዜያት የነበሩ ስራዎች እየታረሙና እየታረቁ በመሄዳቸውም በአሁኑ ወቅት አመርቂ ውጤት እየመጣ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ የኢኮኖሚ ልብ ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 15, 2026 148
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፡- ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ማደግ ለሚያስብ ሀገር ሁሉ በጣም ወሳኝ እና የኢኮኖሚ ልብ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) “የሉዓላዊነት ልብ” በሚል ርዕሰ ጉዳይ ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ጋር ቆይታ አድርገዋል። በቆይታቸውም፤የመደመር መንግሥት መጽሐፍ በፖለቲካና በኢኮኖሚ መካከል ሚዛን መጠበቅ፣ ፖለቲካል ኢኮኖሚን በትክክል መግራትና መረዳት አስፈላጊ ነው ብሎ በሚዛን የሚነሳ መሆኑን አስረድተዋል። አንዱ ገዝፎ አንደኛው ያነሰ እንደሆነ፤ የሚፈለገውን ሥር ነቀል ለውጥ ማምጣት ያስቸግራል ሲሉም አመላክተዋል። ለዚህ ነው የመደመር መንግሥት ሚዛን ጠብቆ ድርሻቸው ሳይዛባ አንዱ ለአንደኛው መከታ ተሸካሚ ሆኖ በጋራ ብልጽግናን ማረጋገጥ እንዲችሉ በትኩረት የተሠራው ብለዋል። ይህ እንዳለ ሆኖ የብዙ መንግሥታት የእኛም ትኩረት ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ላይ የሆነበት ዋናው ምክንያት፤ኢንዱስትሪ ለመለወጥ (ለማደግ) ለሚያስብ ሀገር ሁሉ በጣም ወሳኝ ነገር ስለሆነ ነው ብለዋል። አክለውም፤ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ የኢኮኖሚ ልብ መሆኑን አስገንዝበዋል። አንድ ሰው ልቡ ካልሠራ ሌላው አካላቱ ጤነኛ ቢሆንም ውጤታማ እንደማይሆን ሁሉ፤ ኢኮኖሚን ኢኮኖሚ የሚያደርገው የኢኮኖሚ ልብ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ነው ብለዋል።
ሉዓላዊነትን ለማስጠበቅ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ አይተኬ ሚና አለው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 14, 2026 717
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- ሉዓላዊነትን ለማስጠበቅ፣ የተሻገረ ኢኮኖሚ ለመፍጠር፣ በበቂ ሁኔታ ዜጎችን ሥራ ለማስያዝ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ሚና አይተኬ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “የሉዓላዊነት ልብ” በሚል ርዕሰ ጉዳይ ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ጋር ቆይታ አድርገዋል። በዚሁ ወቅትም፤ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪን አንዳንዶች የዕድገት ሞተር እንደሚሉት አንስተዋል። የዕድገት ሞተር የሚያስብለው ዋናው ምክንያትም፤ ምርታማነትን (ፕሮዳክቲቪቲን) በማሳደግ ረገድ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ያለው ሚና ከሌሎች ሴክተሮች ጋር የሚወዳደር ስላልሆነ ነው ብለዋል። ሌላኛው ምክንያት ደግሞ ወጭ ንግድ (ኤክስፖርት) መሰረት መሆኑን ገልጸው፤ ለኤክስፖርት ብዛትም ጥራትም ወሳኝ መሆናቸውን በማስገንዘብ፤ ብዙ አምርተን፣ በቂ ተጠቅመን ስናበቃ ነው ምንሸጠው ብለዋል። በዚህ ሂደትም ደረጃውን ለጠበቀ ምርት መስፋፋት የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ወሳኝ ሚና አለው፤ ለምርታማነትም ለኤክስፖርትም የዕድገት ሞተር ሆኖ ይወሰዳል ሲሉ አብራርተዋል። ሌላኛው ቁልፍ ምክንያት ደግሞ፤ መዋቅራዊ ሽግግር ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)፤ አንድን የኢኮኖሚ ዘውግ ወደሚቀጥለው የኢኮኖሚ ዘውግ ለመውሰድ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ አይተኬ ሚና አለው ሲሉም በአጽንኦት አንስተዋል። ኢንዱስትሪን የማይጠቀሙ የኢኮኖሚ ዘውጎች ጥሬ ዕቃ አቅራቢ ሊሆኑ ይችላሉ፤ የጥሬ ዕቃ አቅራቢ የሚያደርገው ጉዳይ ፕሮሰስ የማድረግ ዐቅም (ካፓሲቲ) ካልተፈጠረ ነው በማለትም አስረድተዋል። ስለዚህ ከጥሬ ዕቃ ወደ ፕሮሰስ የተሻገረ ዕቃ ለማምጣትም ኢንዱስትሪ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ነው ያስረዱት። ሌላኛው የማኑፋክቸሪንግ ቁልፍ ጉዳይ ፈጠራ እና ቴክኖሎጂ መሆኑን ተናግረዋል። የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ፈጠራን (ቴክኖሎጂን) የሚያመጣው ለራሱ ብቻ አለመሆኑን ገልጸው፤ ለሌሎች ዘርፎችም መሆኑን አስታውቀዋል። በሌላ በኩል ከሥራ ዕድል ፈጠራ አንጻር ያለውን ሚና ገልጸው፤ በማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ የሚፈጠረው የሥራ ዕድል ቁጥር ከፍተኛ ከመሆኑ የተነሳ ከሌሎች ሴክተሮች ጋር እንደማይነጻጸር ጠቁመዋል። በአጠቃላይ ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ሥራ ይፈጥራል፣ ኢኮኖሚ ያሸጋግራል፣ ወደሚቀጥለው ደረጃ ለመሻገር እንደ መስፈንጠሪያ ሆኖ ያገለግላል በማለት አብራርተዋል። በእነዚህ እና በሌሎች ምክንያቶች ማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ የኢኮኖሚ ብቻ ሳይሆን የሉዓላዊነት አንዱ አንጓ ነው፤ አጀንዳ ነው በማለት በአጽንኦት አንስተዋል።
የሴቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ዕውን ለማድረግ የኮሜሳ አባል ሀገራት ያላቸውን የጋራ ትብብር ማጠናከር ይጠበቅባቸዋል
Apr 14, 2026 83
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-የሴቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ዕውን ለማድረግ የኮሜሳ አባል ሀገራት ያላቸውን የጋራ ትብብር ይበልጥ ሊያጠናክሩ እንደሚገባ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሂክማ ኸይረዲን ጥሪ አቀረቡ። በስርዓተ ጾታ እኩልነትና የሴቶች ተጠቃሚነት ላይ ትኩረቱን ያደረገው 15ኛው የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሀገራት የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) ሴክሬታሪያት የቴክኒካል ኮሚቴ አህጉራዊ ስብሰባ መካሄድ ጀምሯል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሂክማ ኸይረዲን በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ የሴቶችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ስትራቴጂ ተቀርፆ ወደ ተግባር ተገብቷል። በዚህም በግብርና፣ በኢንዱስትሪ ዘርፎች በስራ እድል ፈጠራ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል። ሴቶች በንግድ ዘርፍ ላይ በሚፈለገው ደረጃ ሰርተው መለወጥ እንዳይችሉ ማነቆ ከሆኑ ተግዳሮቶች መካከል የፋይናንስ እና የመሥሪያ ቦታ ችግር ተጠቃሽ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ይህን ለመፍታት መንግስት የሚመለከታቸውን አካላት ያሳተፈ ተግባር እያከናወነ መሆኑን አንስተዋል። የአፍሪካውያን ሴቶችን በንግድ ስርዓቱ ላይ ተሳታፊና እኩል ተጠቃሚ ለማድረግ በትብብር መስራት እንደሚገባም ገልጸዋል፡፡ ሴቶች በንግድ ላይ ለመሳተፍ ማነቆ የሆኑባቸውን ተግዳሮት በመፍታት ውጤታማ እንዲሆኑ ለማስቻል የኮሜሳ አባል ሀገራት ተቀራርበን መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡ የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥም የኮሜሳ አባል ሀገራት ያላቸውን ቅንጅታዊ ስራ በይበልጥ ማጠናከር እንደሚገባም ተናግረዋል።   የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሀገራት የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) ረዳት ፀሀፊ አምባሳደር ማህመድ ካዳ በበኩላቸው፤ የሥርዓተ ፆታ እኩልነትንና የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ተግባራት ልማትን ከማሳለጥ ባለፈ አሁጉራዊ ትስስርን የበለጠ ለማጠናከር ያስችላል። ኮሜሳ ሴቶች በማህበራዊ እና በኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ያላቸውን የስርአተ ጾታ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚወጡ አሰራሮችን ለመደገፍ የሚያከናውናቸውን ተግባራት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በአፍሪካ ሴቶች የፋይናንስ፣ የዲጂታል ክህሎት፣ የገበያ፣ የውሳኔ ሰጪነት ያላቸውን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ክፍተቶች መኖራቸውን ጠቁመዋል።   በኮሜሳ ሴክረተሪያት ሲኒየር ጀንደር ሜንስትሪሚንግ ኦፊሰር አንደር ጀንደር ኤንድ ሶሻል አፊር ሴክሬታሪያት ፅጌ ታደለ በበኩላቸው፤ በኮሜሳ አባል ሀገራት ላይ ሴቶችና ወጣቶች በኢኮኖሚያዊ ተግባራት ላይ ያላቸውን ተሳትፎ በማጎልበት ፍትሀዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የሚያስችል ስራ ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካውያን በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው
Apr 14, 2026 349
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በስንዴ ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለአፍሪካዊያን በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት ቦርድ ሊቀ መንበር ኃይለማርያም ደሳለኝ ገለጹ። የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት የተመሰረተበትን 20ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የከፍተኛ ባለሙያዎችና የሥራ ኃላፊዎች ውይይት እየተካሄደ ነው። የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት (አግራ) የአነስተኛ አርሶ አደሮችን በግብዓትና በቴክኖሎጂ በመደገፍ የግብርና እድገትን ለማሳለጥ እንደ አውሮፓውያኑ ዘመን አቆጣጣር በ2006 የተመሰረተ አፍሪካ መር ተቋም ነው።   ተቋሙ የተሻሻለ የዘር ብዜትን፣ የአፈር ጤናማነትን በማስጠበቅና ለግብርና ምርቶችን የገበያ ዕድል በማመቻቸት ዘርፉን በማዘመን የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ግብ ይዟል። የኢትዮጵያ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትርና የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት ቦርድ ሊቀ መንበር ኃይለማርያም ደሳለኝ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ ግብርና ለአፍሪካ የምግብ ዋስትና እና የኢኮኖሚ ዕድገት ለማረጋገጥ የጀርባ አጥንት ነው። አግራ ከ20 ዓመት በፊት ሲቋቋም ለአፍሪካ የስርዓተ ምግብ ዕጣ ፋንታ ወሳኝ የሆነውን ግብርና በማዘመን የዜጎችን ምርታማነት ለማሳደግ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። ግብርና ለአፍሪካ ብልፅግና መሰረት መሆኑን ገልጸው፤ ለስኬታማነቱ የተቋማት ትብብርና ግልፅ የፖሊሲ አተገባበር ያስፈልጋል ብለዋል። ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የግብርና ኤክስቴንሽን ስርዓት በማጠናከርና ቁርጠኛ አመራር በመስጠት ምርትና ምርታማነትን በማሻሻል የወጭ ንግዷን ማሳደግ መቻሏን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ምርትና ምርታማነት እየጨመረ መምጣቱን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ በስንዴ ልማት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች በምሳሌነት የሚጠቀስ ስኬት አስመዝግባለች ብለዋል። ኢትዮጵያ በሰብል ልማት ብቻ ሳይሆን በእንስሳት ሀብት እና ሌሎች የግብርና ዘርፎች የአርሶ አደሮችን ተሳትፎ በማሳደግ በአህጉሪቷ ተጠቃሽ ለውጥ ማምጣቷን ገልጸዋል። በአፍሪካ የግብርና ሽግግር በመፍጠር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ዘላቂ እድገትን ለማስፈን ለችግሮች መፍትሔ ማፈላለግ እንደሚገባም ተናግረዋል። በአፍሪካ የምግብ ስርዓትን ብሔራዊ አጀንዳ ማድረግ ይገባል ያሉት የቦርዱ ሊቀ መንበር፤ አግራ የአፍሪካ ግብርና ሽግግር አቀጣጣይ ሆኖ እያገለገለ ነው ብለዋል። አርሶ አደሩ ዘላቂ የአሰራር ስርዓት እንደሚፈልግ ገልጸው፤ ለሥርዓቱ ቀጣይነት ያለው የተቋማት ትብብር እንደሚያስፈልግ በአጽንኦት ገልጸዋል። በአፍሪካ ህብረት የገጠር ልማት ክፍል እና የግብርናና ምግብ ዋስትና ዘርፍ ኃላፊ ጃኔት ኢደሜ (ዶ/ር)፤ ህብረቱ የምግብ ስርዓትን አሕጉራዊ አጀንዳ አድርጎ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   በአፍሪካ የግብርና ሽግግር ለመፍጠርና የማህበራዊ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትብብር መስራት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። የግብርና ሽግግር የኢኮኖሚ ዕድል ብቻ አይደለም ያሉት ኃላፊዋ፤ የደህንነትና ሉዓላዊነት ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህ ደግሞ አካታች፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር፣ ጠንካራ ተቋማት መገንባትና የፖሊሲ ማዕቀፍ ማውጣት እንደሚገባ አመልክተዋል። የአፍሪካን ትርክት በፈጠራና በጥምረት መገንባት እንደሚገባ ገልጸው፤ ታሪክ ያለፈ ብቻ ሳይሆን ነገን መገንባት ጭምር መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይ 20 ዓመታት አርሶ አደሮችን በማጠናከር ግብርናን ለአፍሪካ ዘላቂ ዕድገትና ልማት መጠቀም እንደሚገባ አብራርተዋል።
በአማራ ክልል በቴክኖሎጂ የታገዘ የገቢ አሰባሰብ ስርዓትን በመተግበር ረገድ የተገኘው ውጤት ልምድ የሚወሰድበት ነው
Apr 14, 2026 127
ባህርዳር ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡- የአማራ ክልል በቴክኖሎጂ የታገዘ የገቢ አሰባሰብ ስርአትን በመተግበር ረገድ የተገኘው ውጤት ልምድና ተሞክሮ የሚወሰድበት መሆኑ ተገለጸ። ‎የአፋር ክልል ገቢዎች ቢሮ፤ የከተማ አስተዳደሮችና ዞኖች የስራ ሀላፊዎች ቡድን ከአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ልምድ ወስደዋል። የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮም በቴክኖሎጂ በታገዘ የገቢ አሰባሰብ ስራው ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ 66 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ መቻሉን አስታውቋል።   ‎የአፋር ክልል ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ አወል አብዲ በጉብኝቱ ላይ እንደገለጹት፤ የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ በአሰራር፣ በአደረጃጀትና በቴክኖሎጂ የተደራጀው አሰራሩ ጥሩ ልምድ የሚወሰድበት ነው። የልምድ ልውውጡም በአፋር ክልል ገቢ አሰባሰብ ስራው ላይ ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ዘመናዊ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂን በመተግበር ፈጣን፣ ግልጽና ተጠያቂነት ያለው አሰራር ለማስፈን የተደረገው ጥረት ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ ለመሰብሰብ መሰረት መሆኑንም ለመገንዘብ መቻላቸውንም ገልጸዋል። የክልሉን ህዝብ የልማትና የሰላም ፍላጎት ለማሟላት የሚቻለው ያለውን ሃብት በአግባቡ በመለየት በተገቢው መሰብሰብ ሲቻል መሆኑንም ገልፀዋል። የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አብዱሙሳ ሁሴን በበኩላቸው፤ የአማራ ክልል በገቢ አሰባሰብ ዘርፍ እያከናወነ ያለው ሁሉን አቀፍ ተግባራትን ለመገንዘብ መቻላቸውን ገልፀዋል።   አሁን ላይ በአሰራር፣ በቴክኖሎጂ አጠቃቀምና ትግበራ እንዲሁም በህግ ማእቀፍ ዝግጅት ያገኙትን ልምድ ወደ ከተማ አስተዳደራቸው ወስደው በመተግበር ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ ለልማት ለማዋል ቁርጠኝነትን እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል። የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ሃላፊ መንገሻ ፈንታው (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት 66 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰብ ተችሏል። በተለይም የ'ኤሌክትሮኒክስ ታክስ አድሚኒስትሬሽን ሲስተም' ተግባራዊ በመደረጉ ትልቅ ውጤት ለማስመዝገብ እንደተቻለም ጠቅሰዋል።   በተጨማሪም ለባለሙያዎች ግንዛቤ በመፍጠር በተሟላ መንገድ እስከታች ድረስ እንዲተገበር መደረጉን አስገንዝበዋል። ‎ይህም ማሕበረሰቡ መብትና ግዴታውን በመገንዘብ የሚጠበቅበትን ግብር በፍትሃዊነት፣ በግልጽነትና ከብልሹ አሰራር በጸዳ መልኩ እንዲከፍል እድል የፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል።
የሴቶችን የንግድ ዘርፍ ተሳትፎ በማሳደግ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Apr 14, 2026 213
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡-ሴቶች በንግድ ዘርፍ ያላቸውን ተሳትፎ በማሳደግ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት በተጠናከረ መንገድ እየተከናወኑ መሆኑን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ። በሥርዓተ ጾታ እኩልነትና የሴቶች ተጠቃሚነት ላይ ትኩረቱን ያደረገው 15ኛው የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሀገራት የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) ሴክሬታሪያት የቴክኒካል ኮሚቴ አህጉራዊ ስብሰባ መካሄድ ጀምሯል። የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሂክማ ኸይረዲን በዚህ ወቅት፤ኢትዮጵያ የገጠርና የከተማ ሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ልዩ ልዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ ትገኛለች ብለዋል። የሴቶችን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ስትራቴጂ ተቀርፆ ወደ ተግባር መገባቱን አውስተው፤በዚህም በግብርና፣በኢንዱስትሪ፣በስራ እድል ፈጠራና በሌሎች ዘርፎች ላይ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል።   የአፍሪካውያን ሴቶችን በንግድ ስርዓቱ ላይ ተሳታፊና እኩል ተጠቃሚ ለማድረግ በትብብር መስራት እንደሚገባ አመላክተዋል፡፡ ሴቶች በንግድ ላይ ለመሳተፍ ማነቆ የሆኑባቸውን ተግዳሮት በመፍታት ውጤታማ እንዲሆኑ ለማስቻል የኮሜሳ አባል ሀገራት ተቀራርበን መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡ የዛሬው ምክክርም ይህን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ነው የተናገሩት። ውይይቱ አፍሪካውያን ሴቶች በንግድ ስርዓቱ ላይ ያላቸውን ተጠቃሚነት ማሳደግ የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ በማዘጋጀት ወደ ተግባር መቀየር የሚቻልበትን እድል የሚፈጥር መሆኑን አንስተዋል። የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሀገራት የጋራ ገበያ(ኮሜሳ) ረዳት ፀሀፊ አምባሳደር ማህመድ ካዳ በበኩላቸው፤ኢትዮጵያ የሥርዓተ ፆታ እኩልነትንና የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማስፈን ለምታሳየው የአመራር ቁርጠኝነት አመሰግነዋል።   እንደ አህጉር የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚሰሩ ስራዎች አበረታች ቢሆንም ቀሪ ስራዎች መኖራቸውን አንስተዋል። በተለይም በአፍሪካ ሴቶች የፋይናንስ፣የዲጂታል ክህሎት፣ የገበያ፣ የውሳኔ ሰጪነት ያላቸውን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አንፃር ክፍተቶች መኖራቸውን ጠቁመዋል። 15ኛው የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሀገራት የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) ሴክሪቴሪያት ቴክኒካል ኮሚቴ አህጉራዊ ስብሰባ እነዚህን ክፍተቶች ለመሙላት ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል፡፡
የመደመር ዕሳቤ ዘመናዊ የአመራረት ሥርዓት ተረጅነትን በማስቀረት የግብርና ምርታማነት ሽግግርን እያፋጠነ ነው
Apr 14, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- የመደመር ዕሳቤ ዘመናዊ የአመራረት ሥርዓት ተረጅነትን በማስቀረት የግብርና ምርታማነት ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ገለጹ። በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በግብርና ሚኒስቴር ትብብር "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዳማ ከተማ የውይይት መድረክ ተካሄዷል።   የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር)፥ የልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር የዜጎችን የምርታማነት ሽግግር እያፋጠነ ነው ብለዋል። በዚህም የልማታዊ ሴፍቲኔት ተጠቃሚ ለነበሩ ዜጎች የሚደረገው የመስኖ ቴክኖሎጂና የግብዓት አቅርቦት ድጋፍ ከተረጅነት ወደ ምርታማነት ማሸጋገር እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የአካባቢ ጥበቃና ሥነ-ምኅዳር ግንባታን በማጠናከር የኢትዮጵያን የዘመናት አሳፋሪ የተረጅነት ታሪክ መስበር እንዳስቻለ አንስተዋል። የዜጎች የሴፍቲኔት ተጠቃሚነት የምርቃት መርሃ ግብር በቀላሉ የሚታይ ሳይሆን ከተረጅነት ወደ ምርታማነት የሚደረግ ወሳኝ የልማት ሽግግር ነው ብለዋል። የመደመር ዕሳቤና ዘመናዊ የአመራረት ሥርዓት ተረጅነትን በማስቀረት የግብርና ምርታማነት ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር አማካሪ ጥላሁን በጅቷል (ዶ/ር)በበኩላቸው፥ አንዳንድ ሀገራት ዕምቅ የመልማት አቅምና ጸጋ ኖሯቸው ሳለ ድህነትን እጣ ፋንታቸው አድርገው እንደሚኖሩ አንስተዋል።   ኢትዮጵያም በሁሉም መስክ ዕድገትና ብልፅግናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ የብዝኅ ጸጋዎች ባለቤት ሆና ሳለ ከድኅነት ጋር ተቆራኝታ እንደቆየች ገልጸዋል። በዚህ መነሻነትም ከሀገራዊ ለውጡ ማግስት የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል የተተገበሩ የፖሊሲ እርምጃዎች የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል አቅም እየተፈጠሩ ነው ብለዋል። በቀጣይም የዜጎችን የሥራ ባህል በመገንባት የብሔራዊ ሀፍረት መነሻ የሆነውን የተረጅነት ታሪክ ለማስቀረት በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ጌቱ ገመቹ፥ በሀገራዊ ለውጡ ማግስት የክልሉን ብዝኅ የግብርና ምርታማነት ምኅዳር በመጠቀም በርካታ ዜጎች ከድኅነት ወደምርታማነት እንዲሸጋገሩ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።   በግብርናው መስክ አርሶና አርብቶ አደሩ የተፈጠረው የሥራ ባህል ለውጥም የምርታማነት ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በቀጣይም የተቋማትን ጠንካራ ቅንጅት በማስቀጠል ሁለንተናዊ የምግብ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ እታገኘሁ አደመ፥ የልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር የአካባቢ ደህንነትን በመጠበቅ የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ ማድረጉን ገልጸዋል።   ይህም የደንና የፍራፍሬ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የዜጎችን ገቢ የማመንጨት አቅም በማሳደግ ከተረጂነት ወደ አምራችነት እያሸጋገረ ነው ብለዋል። በመስኖ መሠረተ ልማት መርሃ ግብርም በርካታ ዜጎች የምግብ ዋስትናቸውን እንዲረጋገጥ እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል።  
በኦሮሚያ ክልል በመስኖ ልማት የአርሶ አደሩን የስራ ባህል መለወጥ ተችሏል
Apr 14, 2026 105
አዲስ አበባ ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ለመስኖ ልማት በተሰጠው ትኩረት በአርሶ አደሩ ዘንድ 'ክረምት አርሶ በጋ ማረፍ' የሚለውን አመለካከት መለወጥ መቻሉን የክልሉ የመስኖ እና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ገለጸ። የቢሮው ኃላፊ ኢንጂነር ግርማ ረጋሳ፤ የክልሉ መንግሥት ባለፉት የለውጥ ዓመታት ግብርናን ለማዘመን የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራትን አከናውኗል ብለዋል።   ከእነዚህ ሥራዎች መካከል ቀደም ሲል እምብዛም ትኩረት ያልተሰጠውን የመስኖ ልማት ሥራ በመሠረታዊነት መለወጥ ያስቻሉ ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። በተለይም በክልሉ ቆላማ አካባቢዎች በተከናወኑ የመስኖ ልማት ሥራዎች የአርብቶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ጭምር እያገዘ መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ መንግሥት የመስኖ ልማትን ለማስፋፋት ዘመናዊ የመስኖ አጠቃቀምን ማዳበርና አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ግድቦች ግንባታን ማከናወን መቻሉንም ጠቁመዋል። ይህ ብቻ ሳይሆን የክልሉ መንግስት 3 ቢሊዮን ብር በጀት በመመደብ የውኃ መሳቢያ ሞተሮችን ጨምሮ ለመስኖ ልማት የሚያግዙ ቴክኖሎጂዎችን ለአርሶ እና አርብቶ አደሩ እንዲቀርቡ መደረጉን አስረድተዋል። ባለፉት ጥቂት ዓመታት ብቻ ከ200 በላይ የመስኖ መሠረተ ልማቶች መገንባታቸውን ጠቅሰው፤ "ፊነ" በተሰኘ በክልሉ ቆላማ አካባቢ ልማት ላይ በሚሠራ ፕሮጀክት አማካኝነትም የተሻለ ሥራ መሠራቱን ገልጸዋል። በ"ፊነ" ፕሮጀክት አማካኝነት በክልሉ ቆላማ እና አርብቶ አደር አካባቢዎች የተገነቡ የውሃ ጉድጓዶችና አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ግድቦች ትልቅ ተስፋ የሰጡ መሆናቸውንም ተናግረዋል። ለአብነትም በቦረና አካባቢ የተገነቡ አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ግድቦች አርብቶ አደሩ ማኅበረሰብ ድርቅን መቋቋም እንዲችል እያገዙት ሲሆን፤ ለእንስሳት መጠጥ እና ለመኖ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛሉ ብለዋል። በአጠቃላይ በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ ሥራዎች 70 ሺህ ሄክታር የነበረው የመስኖ ልማት ሽፋን በዚህ ወቅት ከ3 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መድረሱን ገልጸዋል። ከሁሉም በላይ የክልሉ መንግሥት ለመስኖ ልማት በሰጠው ልዩ ትኩረት በአርሶ አደሩ ዘንድ የነበረውን "ክረምት አርሶ በጋ የሚያርፍበትን" አሮጌ አመለካከት መለወጥ ተችሏል ብለዋል። በዚህም የክልሉ አርሶ እና አርብቶ አደር ዓመቱን ሙሉ የግብርና ሥራ እያከናወነ የምግብ ዋስትናውን ማረጋገጥ እንዲችል የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ጠቁመዋል።
በዞኑ በበልግ ወቅቱ ከ92 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር ተሸፍኗል
Apr 14, 2026 100
ደሴ፤ ሚያዚያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ወሎ ዞን እየጣለ ያለውን የበልግ ወቅት ዝናብ በመጠቀም ከ92 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ይመር ሰይድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው። በዚህም በበልግ ወቅቱ ከ104 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከ1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በተደረገ ጥረት ከ92 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር መሸፈኑን ጠቁመው ከተዘራው ውስጥ ስንዴ፣ ገብስ፣ ጤፍ፣ ቦለቄ፣ ማሾ፣አተር፣ ምስርና ሌሎች ሰብሎች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል። እቅዱን ለማሳካትም እስከ ሚያዚያ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎች ላይ በማተኮር የዘር ስራው ተጠናክሮ መቀጠሉን አስገንዝበዋል። በቀጣይም አርሶ አደሩ የሰብሉን ሁኔታ በመከታተል የአረምና የተባይ ቁጥጥር ስራ እንዲያከናውን የባለሙያ ድጋፍ እንደሚደረግ አመላክተዋል። የበልግ ልማቱን ምርታማነት ለማሳደግም ለአርሶ አደሩ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ቀድሞ መቅረቡን ተናግረዋል። በዞኑ ተሁለደሬ ወረዳ የቀበሌ 01 ነዋሪ አርሶ አደር አህመድ መሀመድ በበኩላቸው፣ የዘንድሮው የበልግ ዝናብ ለሰብል ልማት ምቹ በመሆኑ አንድ ሄክታር ተኩል ማሳቸውን በስንዴና በጤፍ ማልማታቸውን ጠቁመዋል። ለስራው ስኬትም የግብርና ግብዓት በወቅቱ ማግኘታቸውን ጠቁመው ሰብሉን በተገቢው በመንከባከብ ጥሩ ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም አንድ ሄክታር ማሳቸውን በስንዴና ገብስ ዘር መሸፈናቸውን የተናገሩት ደግሞ በኩታበር ወረዳ የቀበሌ 03 ነዋሪ አርሶ አደር ይመር ሰይድ ናቸው። የሰብሉ ቡቃያ ያማረ በመሆኑ ከአረምና ከተባይ የመጠበቅ ስራ እያከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል።  
የበጋ ስንዴ ልማት አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለገበያ የሚሆን ምርት ለማቅረብ አስችሏል
Apr 14, 2026 96
ጎንደር ፤ሚያዚያ 6/2018 (ኢዜአ)፡-በማእከላዊ ጎንደር ዞን የተካሔደው የበጋ ስንዴ ልማት ስራ አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለገበያ የሚሆን ምርት ለማቅረብ ማስቻሉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ በዞኑ ዘንድሮው በተካሄደው የበጋ ወቅት የመስኖ ስንዴ ልማት ስራ ከአንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ የስንዴ ምርት ለገበያ ማቅረብ መቻሉም ተገልጿል፡፡ በመምሪያው የመስኖ ልማት ቡድን መሪ አቶ ሀውልቱ ታደሰ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ኢንሼቲቭ አርሶ አደሩ ዓመቱን ሙሉ የሚያመርትበትን አዲስ የስራ ባህል ፈጥሯል። በዞኑ ከአራት ዓመት በፊት በበጋ መስኖ ስንዴ የሚለማው መሬት ከአራት ሺህ ሄክታር የማይበልጥ፤የሚገኘው ምርት ደግሞ ከ112 ሺህ ኩንታል የዘለለ እንዳልነበረ አስታውሰዋል። በዘንድሮ የበጋ ወቅት ደግሞ ከ29 ሺ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ዓመታዊ ምርቱን ከአንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ለማድረስ መቻሉን ገልጸዋል። የበጋ ስንዴ ልማት ስራ አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ ባለፈ ለአግሮ ኢንዱሰትሪዎች ግብአትና ለገበያ የሚሆን ምርት በማምረት ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ ማስቻሉን ነው የገለጹት፡፡ በዚሁ ወቅት አርሶ አደሩ ምርታማነትን እንዲያሳድግም አዳዲስና ዘመናዊ የግብርና አሰራሮችንና ቴክኖሎጂዎችን በስፋት ተግባራዊ እንዲያደርግም የባለሙያዎች እገዛ ከፍተኛ አስተዋጽአ ማበርከቱን ነው የተናገሩት። የኩታ ገጠም እርሻ፤ የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ተሞክሮችን በመጠቀም በዘላቂነት ምርታማነትን ለማሳደግ እንዲቻል በትኩረት መሰራቱን አስረድተዋል። በዞኑ የወገራ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር መላኩ ቸርነት ፤ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ስራ ለራስ ፍጆታ ብቻ የነበረውን አመራረት በመቀየር ለገበያ የሚተርፍ ምርት ማግኝት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። በዘንድሮ በጋም በአንድ ሄክታር መሬት ካለሙት የስንዴ ሰብል 36 ኩንታል ስንዴ በማምረት ለገበያ አቅርበው ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የሚገልጹት፡፡ በምእራብ ደንቢያ ወረዳ የዋዋ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር የሻምበል መንግስቱ በበኩላቸው፤ በዘንድሮው በጋ በግማሽ ሄክታር መሬት ላይ በመስኖ ካለሙት የሰንዴ ሰብል 18 ኩንታል ምርት አግኝተዋል። ያገኙት ምርትም ከራሳቸው አልፎ ለገበያ ለማቅረብ መቻላቸውን ነው ያስታወቁት።    
በሐረሪ ክልል በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር አበረታች ውጤት ተመዝግቧል
Apr 14, 2026 96
ሐረር ፤ ሚያዝያ 06/2018 (ኢዜአ) ፦ በሐረሪ ክልል እየተከናወነ ባለው የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር አበረታች ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የእንሰሳት ሃብት ልማት ዳይሬክተር ናኦል አብዱማሊክ ለኢዜአ እንደገለጹት ባለፉት ዓመታት በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር በተከናወኑ ተግባራት በእንስሳት ሀብት ልማትና ምርታማነት ላይ አበረታች ውጤት ተመዝግቧል።   በዚህም የወተት ምርትን በማሳደግ፣ የእንቁላልና የማር ምርት አቅርቦትን በማሻሻል ረገድ ተጨባጭ ውጤት መታየቱን ጠቁመዋል። የክልሉ መንግስት ከፍተኛ በጀት በመመደብ የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብርን ማበረታታቱን አንስተው፤ በበጀት ዓመቱ ባለፉት 9 ወራትም 12 ሼዶችን በከተማና በገጠር በመገንባት ወደ ስራ መግባታቸውን ገልጸዋል። እንዲሁም የእንስሳት መኖ አቅርቦትን የማጎልበት ተግባራት መከናወኑንም አብራርተዋል። በዶሮ እርባታም በበጀት ዓመቱ 12ሺህ የዶሮ ጫጩቶችን ለህብረተሰቡ የማሰራጨት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው፤ በዚህም የህብረተሰቡ ፍላጎት እያደገ በመምጣቱ በራቱ ተነሳሽነት ግዢ እየፈጸመ መሆኑን አስረድተዋል። ምርቱም በከተማው የቅዳሜና እሁድ ገበያ በተመጣጣኝ ዋጋ በስፋት እየቀረበ እንደሚገኝም አስረድተዋል። በክልሉ በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር የተለያዩ ዘርፎች ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ በዘርፉ የተሰማሩ አርሶ አደሮችና ሌሎች ግለሰቦች ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ገልጸዋል። በተለይም በዘርፉ ለወጣቶች የስራ እድል ከመፈጠሩ ባለፈ ገበያን በማረጋጋት ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ጠቁመዋል።
ከተረጅነት ወደ ምርታማነት ፍኖተ ካርታ ትግበራ ድህነትን በመግታት ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው
Apr 14, 2026 215
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ የተረጅነት ታሪክን ወደ ምርታማነት የማሸጋገር ፍኖተ ካርታ ትግበራ ድህነትን በመግታት ረገድ ውጤት እያስገኘ መሆኑን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር) ገለጹ። በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በግብርና ሚኒስቴር ትብብር "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዳማ ከተማ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   በመድረኩም በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር)፥ "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት ለተሟላ ሀገራዊ ሉዓላዊነትና ክብር" በሚል ርዕሰ ጉዳይ ላይ የመነሻ ጽሁፍ አቅርበዋል። በመነሻ ጽሁፋቸውም፥ ኢትዮጵያ በቀደምት ጀግኖች ሉዓላዊነቷን አስጠብቃ የቆየች ሀገር ናት ብለዋል። ኢትዮጵያ ሉዓላዊነቷን አስጠብቃ የቆየች ሀገር ብትሆንም ተረጅነትና ልመናን ለማስቀረት የነበረው የታሪክ ስብራት የተሟላ ሉዓላዊነትን ማጎናጸፍ ሳይችል እንደቆየ አስረድተዋል። በዚህም ከሀገራዊ ለውጡ ማግስት የኢትዮጵያን የተሟላ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የተወሰዱ የፖሊሲ እርምጃዎች ዜጎችን ክብር እያጎናጸፉ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በአየር ንብረት ለውጥና ተያያዥ ጉዳዮች ኢትዮጵያ በድርቅና ርሃብ አደጋ ፈተናዎችን በመቀልበስ እመርታዊ የምርታማነት ሽግግር መደረጉን ተናግረዋል። የተረጅነት አስተሳሰብን ማስቀረትም ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ክብር የላቀ ትርጉም የሚሰጠው መሆኑን አንስተዋል። የራስ የምርታማነት አቅም በመፍጠር ለአደጋ የማይበገር ማህበረሰብ መገንባት እየተቻለ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።   ይህም የኢትዮጵያን የተሟላ የሉዓላዊነት ፈተናዎች በመቀልበስ የተፈጠረው የምርታማነት አቅም የሀገርን አይበገሬነት በተግባር ያስመሰከረ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያን የተረጅነት ታሪክ ወደ ምርታማነት ለማሸጋገርም መግባባት፣ ማጥራት፣ ማዘጋጀት፣ ማቀናጀትና ማሸጋገር ፍኖተ ካርታ ትግበራ ድህነትን በመግታት ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መሆኑን አስገንዝበዋል። የልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብርም በርካታ ዜጎችን ከድህነት በማላቀቅ የትርፍ አምራችነት ሽግግርን እያፋጠነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በቀጣይም የብልፅግና ፓርቲ አመራርና አባላት፣የመንግሥት የስራ ኃላፊዎችና ሙያተኞች፣ የልማት አጋሮች፣ መገናኛ ብዙኅንና ህዝቡ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተመዘገበውን ስኬት የማስቀጠልና የማፅናት ኃላፊነታቸውን ማስቀጠል እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል።
የግብርና ምርምር ተቋማት በመደመር እሳቤ ቅንጅታቸውን ሊያጠናክሩ ይገባል
Apr 14, 2026 122
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ የግብርና የምርምር ተቋማት በመደመር እሳቤ ያላቸውን ትስስርና ቅንጅት ሊያጠናክሩ እንደሚገባ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር) ገለፁ። የግብርና ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት እና ከኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ጋር በመተባበር የተዘጋጀ በብሔራዊ የግብርና ምርምር ሥርዓቶች ላይ ያተኮረ ውይይት ተካሄዷል።   ውይይቱ "በኢትዮጵያ ብሔራዊ የግብርና ምርምር ሥርዓቶችን እንደገና ማጤን፤ተቋማዊ ውህደት፣ ስትራቴጂካዊ ቅንጅት እና የውጤታማነት መንገዶች" በሚል መሪ ሃሳብ ተካሄዷል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ ባለፉት አሥርት ዓመታት በግብርና ዘርፍ ለምርምር ስራዎች በሰፊ ኢንቨስት ተደርጓል። የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት፣ የክልል ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩቶች፣ ዩኒቨርሲቲዎች እና ዓለም አቀፍ የምርምር አጋሮች እውቀትን፣ ቴክኖሎጂን እና ፈጠራን በማመንጨት ረገድ ወሳኝ ሚና መጫወታቸውን ጠቅሰዋል። እነዚህ ጥረቶች ለምርታማነት እድገት፣ ለቴክኖሎጂ እና ለአቅም ግንባታ ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ተናግረዋል። ይሁን እንጂ የምርምር ሥርዓቱ ሙሉ አቅሙን እንዳይጠቀም ተቋማዊ መበታተን፣ ደካማ ቅንጅት እና የምርምር ውጤቶች ወደ ተግባር ተቀይረው አርሶ አደሩ ዘንድ የመድረስ ውስንነት ተግዳሮቶች እንዳሉ ጠቁመዋል። ይህን ለማቃለል የምርምር ሥርዓቱ በመደመር ዕሳቤ ሊቃኝ እንደሚገባ ተናግረው፤ ተቋማት በተናጠል ከመሥራት ይልቅ በቅንጅት እንዲሠሩ፣ ሳይንስ ከፖሊሲ ጋር እንዲተሳሰር እና በምርምር የሚገኘው ዕውቀት በአርሶ አደሩ ሕይወት ላይ ለውጥ ማምጣት እንደሚያስችል ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ዋና ስራ አስፈፃሚ ፕሮፌሰር ተከተል ዮሐንስ በበኩላቸው፤ አካዳሚው በስድስት ዋና ዋና የሥራ ዘርፎች ተከፋፍሎ ተግባራቱን እያከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   አካዳሚው በብቃትና በላቀ የሙያ ተሳትፎ ላይ የተመሰረተ ማህበር እንደመሆኑ የግብርና የሥራ ቡድን ከ70 በላይ አባላትን በመያዝ ከአካዳሚው ግዙፍና ቀዳሚው የሥራ ዘርፍ እንደሆነ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ንጉሤ ደቻሳ በበኩላቸው እንዳሉት፤ የግብርና ምርምር ስራዎች ውጤታማና ሀገራዊ ፋይዳ ያላቸው እንዲሆኑ የተቀናጀ አሰራርና ብሔራዊ ስትራቴጂ መቅረጽ አስፈላጊ ነው።   የግብርና ልማቱን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ስልታዊ ለሆኑ ጉዳዮች ቅድሚያ የሚሰጥ የጋራ መመሪያ መኖር እንዳለበትም አመልክተዋል። የቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር ታምራት ደገፋ (ዶ/ር)፤ በምርምር ተቋማት መካከል አዲስ ተቋማዊ ውህደትና የአፈጻጸም መለኪያ አስፈላጊነትን አንስተዋል።   የምርምር ሥራችንም ሆነ ግባችንን በማሳካት ረገድ ስኬታማ መሆን አለመሆናችንን የምንለካባቸው ቁልፍ የአፈጻጸም አመልካቾች መዘጋጀት አለባቸው ሲሉ ተናግረዋል። የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ምሁር ፕሮፌሰር ፍሬው መክበብ እንደተናገሩት፤ ዘርፉን በአግባቡ መምራት የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍ ማዘጋጀት ይገባል።   ይህ ብሔራዊ ምርምርን በብቃት መምራት እንደሚያስችል ገልጸው፤ ለዘርፉ አስፈላጊውን በጀት መመደብ እንደሚገባ ተናግረዋል። የዓለም አቀፍ የግብርና ምርምር አማካሪ ቡድን የአፍሪካ ግንኙነት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ናበሙኮሎ ኮቪክ (ዶ/ር) በግብርና ዘርፍ ያሉ የምርምር ተቋማት በተወሰኑ ዘርፎች ላይ በሚያተኩሩ የልህቀት ማዕከላት እንዲደራጁ ሐሳብ አቅርበዋል።   የዘርፉን ውጤታማነት ይበልጥ ለማረጋገጥ የሚደረገው ቅንጅት በበቂ በጀት ሊደገፍ እንደሚገባም ተናግረዋል።
የግብርናው ዘርፍ ምርታማነት የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል አቅም እየፈጠረ ነው
Apr 14, 2026 224
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ከሀገራዊ ለውጡ ማግስት በግብርናው ዘርፍ የተከናወኑ የሪፎርም ሥራዎች የምርታማነት አቅምን በከፍተኛ ደረጃ በማሳደግ የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የሚያስችል አቅም እየፈጠረ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) ገለጹ። በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በግብርና ሚኒስቴር ትብብር "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዳማ ከተማ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር)፥ የለውጡ መንግሥት በብዝኅ የኢኮኖሚ ሥርዓት የግብርና ምርታማነትን የሚያሻሽሉ የፖሊሲ እርምጃዎች ተወስደዋል ብለዋል። በዚህም በአጭር ጊዜ ውስጥ በሁሉም መስክ የተኪ ምርት አቅምን በማሳደግ የወጪ ንግድ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ማሳደጉን ጠቅሰዋል። የግብርና ዘርፍ በዝናብ ጥገኝነት ላይ የተንጠለጠለና የዜጎችን የምግብ ሉዓላዊነት ፈታኝ አድርጎት ቆይቶ እንደነበር አስታውሰዋል።   የአየር ንብረት ለውጥና የአካባቢ ደህንነት መመናመንም በተለያዩ ወረዳዎች ላይ የሚኖሩ ዜጎች የእርዳታ ጥገኛ ሆነው እንደቆዩ አስረድተዋል። በአጭር ጊዜ ተግባራዊ የተደረጉ የፖሊሲ እርምጃዎችና የሴፍቲኔት ልማታዊ መርሃ ግብር በርካታ ዜጎችን የግብርና ምርታማነት በማሳደግ ከተረጅነት ወደ ምርታማነት ማሸጋገር እንደተቻለ አብራርተዋል። በዚህም በሁሉም የግብርና መስክ የተፈጠረው የምርታማነት አቅም የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የሚያስችል አቅም እየተፈጠረ መሆኑን አንስተዋል።   የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሰይፈ ደርቤ በበኩላቸው፥ መገናኛ ብዙኅን በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታና በተለያዩ የልማት ስራዎች ላይ ወሳኝ አጀንዳ በመቅረፅ ሰፊ ስራ እየሰሩ ነው ብለዋል። ኢዜአም የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የኢትዮጵያን የተረጅነት ታሪክን በማስቀረት የምግብ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ የዜጎችን ክብር የሚያጎናጽፍ ድል እየተመዘገበ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "የግብርና ምርታማነት ለምግብ ሉዓላዊነትና ለሀገራዊ ክብር" በሚል መሪ ሀሳብ በለውጡ ዓመታት በግብርናው ዘርፍ የተገኙ ውጤቶች ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ መጋቢት 23 ቀን 2018 ዓም ማካሄዱ ይታወቃል፡፡  
"ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዳማ ከተማ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል
Apr 14, 2026 183
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በግብርና ሚኒስቴር ትብብር "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዳማ ከተማ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ እውነቴ አለነ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር)፣ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) እና የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ተገኝተዋል።   በተጨማሪም የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሰይፈ ደርቤ፣ የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ጌቱ ገመቹ ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የፌደራልና የክልል ግብርና ቢሮ የሥራ ኃላፊዎችና የግብርና ሙያተኞች ተገኝተዋል። በመድረኩም የኢትዮጵያን የግብርና ምርታማነት በማስቀጠል የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ የመነሻ ሃሳቦች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል ተብሎ ይጠበቃል። ኢትዮጵያ በበጋ መስኖ ስንዴ፣ በመኸርና በበልግ ወራት የሰብል ምርታማነት፣በሌማት ትሩፋት እና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል እመርታዊ ውጤት በማስመዝገብ ላይ ትገኛለች።   ለአብነትም የዘመናት ተረጅነትን በማስቀረት ከራስ አልፎ ስንዴን ወደ ውጪ በመላክ ወደተሟላ ሀገራዊ ክብር መሸጋገር የሚያስችል የታሪክ ምዕራፍ ላይ ትገኛለች።
በምስራቅ ቦረና ዞን በበልግ አዝመራ ከ160 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Apr 14, 2026 92
ነገሌ ቦረና፤ሚያዝያ 6/ 2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ቦረና ዞን ቆላማ ወረዳዎች በዘንድሮው የበልግ አዝመራ ከ160 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። ምስራቅ ቦረና ቆላማና ዝናብ አጠር ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በብዛት የእንስሳት እርባታ የሚካሄድበት ቢሆንም፤ከመጋቢት 15 እስከ ሚያዝያ አጋማሽ ያለው ጊዜ ዋነኛው የበልግ ዝናብና የእርሻ ወቅት መሆኑ ተገልጿል። በጽሕፈት ቤቱ የሰብል ልማትና ጥበቃ ባለሙያ አቶ ቦነያ ሁቃ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው የበልግ ወቅት 176 ሺህ 223 ሄክታር መሬት ታርሶ ለዘር ተዘጋጅቷል። በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች ለበልግ አዝመራ ከተዘጋጀው መሬት ውስጥ እስካሁን 160 ሺህ 539 ሄክታር የሚሆነው በአራት ዋና ዋና ሰብሎች መልማቱን ገልጸዋል። በቆላማ ወረዳዎቹ የታረሰው መሬት በስንዴ፣ በጤፍ፣ በበቆሎና በቦለቄ ምርጥ ዘር እየለማ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዚህ የበልግ አዝመራ 137 ሺህ 324 አርሶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮች በመሳተፍ ላይ ሲሆኑ፤ ከእነዚህም መካከል 20 ሺህ 297 ያህሉ ሴቶች መሆናቸውን ገልጸዋል። በዞኑ በበልግ አዝመራ ከሚለማው መሬት በአጠቃላይ ከ3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዷል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም