ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 181
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ የሕዝብ ጤናን እየጠበቅን፣ የነዋሪዎችን መተዳደሪያ አቅም እያጠናከርን መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ግዙፉ የቦረና የመጠጥ ውኃ አቅርቦትፕሮጀክት ለኅብረተሰቡ አስተማማኝ የንጹሕ ውኃ አቅርቦት ተደራሽ በማድረግ፣ በምሥራቅ ቦረና እና በቦረና ዞኖች የሚገኙ ነዋሪዎችን ሕይወት እየቀየረ ይገኛል ብለዋል። በብዙ ኪሎ ሜትሮች የሚቆጠሩ የቧንቧ መስመሮችን፣ ዘመናዊ የውኃ ማከፋፈያ ጣቢያዎችን እና ሰፋፊ የውኃ ማጠራቀሚያዎችን ያካተተ ዘላቂ መሠረተ ልማት እየገነባን ሲሆን ይህም ድርቅን ከመመከት የላቀ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት የሕዝብ ጤናን እየጠበቅን፣ የነዋሪዎችን መተዳደሪያ አቅም እያጠናከርን መጪው ትውልድ የሚጠቀምበትን የግብርና እምቅ አቅም እያዘጋጀን እንገኛለን ብለዋል።
በአዳማ ከተማ በተለያዩ ዘርፎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነዋሪዎች ውጤታማ በመሆናቸው ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል ፈጥረዋል
May 27, 2026 133
አዳማ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ በአዳማ ከተማ በተለያዩ ዘርፎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነዋሪዎች ውጤታማ በመሆናቸው ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ገለጹ። ከተጠቃሚዎቹ መካከል አቶ ጌቱ ተስፋዬ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ከተማ አስተዳደሩ በቤተሰብ ብልጽግና ተደራጅተው ራሳቸውንና ማኅበረሰቡን ተጠቃሚ እንዲያደርጉ ከፍተኛ ድጋፍ እንዳደረገላቸው ገልጸዋል። በከተማዋ ቦሌ ክፍለ ከተማ በተመቻቸላቸው የመሥሪያ ቦታ ላይ ከአምስት የቤተሰብ አባላት ጋር በመደራጀት በዚህ ዓመት ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል። መንግሥት ባመቻቸላቸው የ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ብድር በዳቦ ማምረቻ ኢንተርፕራይዝ ተደራጅተው ምርታቸውን ለአካባቢው ማኅበረሰብ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን አስረድተዋል። አሁን ላይ ከራሳቸው አልፈው ለ10 ተጨማሪ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን አውስተዋል። ሌላኛው በዱቄት ማምረቻ ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ገዙ በዳዳ በበኩላቸው፤ መንግሥት ወደ ልማት እንዲገቡ እንዲሁም ተጠቃሚ እንዲሆኑ ትልቅ እገዛ ማድረጉን ገልጸዋል። ከተማ አስተዳደሩ የመሥሪያ ቦታ ከመስጠትና መሠረተ ልማት ከማሟላት ባለፈ፣ ከባንክ የ2 ሚሊዮን ብር ብድር እና የካፒታል ማሽን አቅርቦት እንዲያገኙ በማመቻቸት በሙሉ አቅማቸው ወደ ሥራ እንዲገቡ ድጋፍ ማድረጉን አመልክተዋል። አቶ ገዙና የቤተሰባቸው አባላት የዱቄት ማምረቻ ማኅበር በቀን 330 ኩንታል የስንዴ ዱቄት በማምረት ለዳቦ ፋብሪካዎችና ለኅብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ ይገኛሉ ብለዋል። በዚህም ውጤታማ መሆን ከመቻላቸው ባለፈ ለስምንት ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ገልጸዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው፤ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የቤተሰብ ብልጽግና ፓኬጅ በከተማዋ በተደራጀ መልኩ ተግባራዊ እየተደረገ ነው ብለዋል። ይህ አሠራር እያንዳንዱን ቤተሰብ ለለውጥና ለዕድገት በማነቃቃት፣ ለመበልፀግ በቁጭት እንዲነሱ ማድረጉን ጠቁመው፤ ተሳታፊዎች የጠራ ግንዛቤ ይዘው ሥራ ውስጥ እንዲገቡ እየተደረገ ይገኛል ነው ያሉት። በበጀት ዓመቱ ለቤተሰብ ብልጽግና ተሳታፊዎች የሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን የጠቀሱት ከንቲባው፤ ለዚህም አስተዳደሩ የመሥሪያና የመሸጫ ቦታዎችን እንዲሁም የብድር አቅርቦትን ለማመቻቸት እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህ ዓመት በከተማዋ በተገነቡ በርካታ ሼዶች 89ሺህ የከተማዋ ወጣቶችና ነዋሪዎች በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዘርፎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆን ችለዋል ብለዋል።
ሀዋሳ ከተማን ለነዋሪዎች ምቹ እና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጠናክሮ ይቀጥላል
May 27, 2026 116
ሀዋሳ፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን ለነዋሪዎች ምቹ እና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ከከተማው ከንቲባና ከተለያዩ ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች ጋር በመሆን፤ በከተማዋ ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በምረቃው መርሃ ገብር እንዳሉት፤ የለውጡ መንግስት ለከተሞች በሰጠው ልዩ ትኩረት የከተሞችን ዕድገት የሚያፋጥኑ ዘርፈ-ብዙ የልማት ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በዚህም ሀዋሳን ለነዋሪዎቿ ምቹ፣ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት ደግሞ ተመራጭ ለማድረግ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ቀጣይነት ለማረጋገጥ ህብረተሰቡን ያሳተፈ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል። በከተማዋ የተመረቁት የልማት ፕሮጀክቶች በኮሪደር ልማት የተጀመሩ ሥራዎችን ከማጠናከር ባለፈ፤ የአገልግሎት አሰጣጥን በማሳለጥ የሕዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች የሚመልሱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የክልሉ መንግስት ሀዋሳን የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ ለቱሪዝም መስህብ ልማቶችና ለአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ማስፋፊያ ልዩ ትኩረት መስጠቱንም አንስተዋል። የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው፤ የሀዋሳን የኮሪደር ልማትና ሁሉን አቀፍ የልማት ፕሮጀክቶች በማፋጠን ከተማዋን የቱሪዝምና የኢንዱስትሪ ማዕከል ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በከተማዋ በመደመር እሳቤ የሚከናወኑት የልማት ፕሮጀክቶች በተለይም በጥራት ላይ ማተኮራቸውን አብራርተዋል። ዛሬ ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የአዳሬ አጠቃላይ ሆስፒታል ማስፋፊያ፣ የአጠቃላይ ትምህርት ቤቶች ማስፋፊያ ግንባታ እና ሌሎች መሰረተ-ልማቶች ይገኙበታል ብለዋል። እነዚህ ፕሮጀክቶች በአጠቃላይ ከ2 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው መሆኑን ከንቲባው አስታውቀዋል። የሃዋሳ ከተማ ነዋሪዋ ሲስተር እልፍነሽ ናኡሼ፤ በሃዋሳ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች ከተማዋን አዲስ ገጽታ እያላበሷት መሆኑንና የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች አዲስ የሥራ ዕድል እየፈጠሩ እንደሚገኙ አክለዋል። ሌላኛው የከተማው ነዋሪ አቶ ተስፋዬ አበባው፤ ዛሬ በከተማዋ የተመረቁት ፕሮጀክቶች በተለይም በጤናው ዘርፍ የነበሩትን ውስንነቶች ከመቅረፍ አንጻር ትልቅ ሚና እንደሚኖራቸው ገልጸዋል። በምረቃ መርሃ-ግብሩ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር)፣ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎችና የሕብረተሰብ ተወካዮች ተገኝተዋል።
የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የበለጠ ያነቃቃል
May 27, 2026 109
ነገሌ ቦረና፤ ግንቦት 19/2018(ኢዜአ)፦ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ የበለጠ የሚያነቃቃ መሆኑን የዞኑ ነዋሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የሀገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውንና አዲሱን የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያን ዛሬ በይፋ መርቀዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው እንደ ቦይንግ 737 ማክስ ያሉ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን የማስተናገድ አቅም ያለው ይህ ዘመናዊ አውሮፕላን ማረፊያ፤ የአካባቢውን እንዲሁም ድንበር ተሻጋሪ የንግድ ልውውጥን እና ቱሪዝምን የማሳደግ ራዕይን ሰንቆ በሳምንት ሦስት በረራዎችን የሚያስተናግድ ነው ብለዋል። በምስራቅ ቦረና ዞን የተገነባው ይኸው የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑ፣ ምቹ፣ ፈጣንና ቀልጣፋ የትራንስፖርት አገልግሎት ለማግኘት እንደሚያስችላቸው የዞኑ ነዋሪዎች ገልጸዋል። የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪው እንዳለ መገርሳ እንደገለጹት፤ የአውሮፕላን ማረፊያው በየብስ ትራንስፖርት ረጅም ጉዞ ምክንያት ይደርስ የነበረውን እንግልትና ችግር በእጅጉ ያቃልላል። ዞኑ በእንስሳት ሀብትና የስንዴ ምርት የሚታወቅ ቢሆንም፣ ምርቱን ለማጓጓዝ የትራንስፖርት እጥረት ያጋጥም እንደነበር አስታውሰው፣ አውሮፕላን ማረፊያው የምርት ዝውውርን የበለጠ ያቀላጥፋል ብለዋል። ይህም ለአካባቢው ኢኮኖሚና ቱሪዝም እድገት ካለው አስተዋጽኦ ባሻገር የመንገደኞችን ጉዞ ምቹ፣ ቀላልና ፈጣን እንደሚያደርገው ገልጸዋል። በዘመናዊ ትራንስፖርት ለመጠቀም የነበራቸው ምኞት በመሳካቱ መደሰታቸውን ተናግረዋል። ሌላው የነገሌ ቦረና ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ ፈንታ ገረመው በበኩላቸው፤ የአውሮፕላን ማረፊያው ስራ መጀመር የዞኑን ልማትና እድገት እንደሚያፋጥን ገልጸዋል። በተለይም የነገሌ ቦረና ከተማን የንግድና የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አብራርተዋል። ሌላው በዞኑ ሊበን ወረዳ ነዋሪ ቢሉ ቢርቢርሳ የአውሮፕላን ማረፊያው መንግስት ለአርብቶ አደሩ አካባቢ የሰጠውን ትኩረትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት በተግባር ያረጋገጠ መሆኑን አንስተዋል። ለአካባቢው ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል እንደሚፈጥር፣ የግብርና ምርቶችና ግብአቶች በወቅቱና በፈጣን ሁኔታ እንዲጓጓዙ እንደሚረዳና ባለሀብቶች እንዲሁም ተጓዦች ወደ ዞኑ በቀላሉ እንዲመጡ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ጠቅሰዋል። በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ የሀገር ሽማግሌዎች፣ አባገዳዎች፣ የፌደራል፣ የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በርካታ ቁጥር ያለው የዞኑ ህዝብ ተገኝቷል።
የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ መመረቅ ፍትሐዊና ሚዛናዊ የመሠረተ ልማት ዝርጋታን የሚያረጋግጥ ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 169
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፦ የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ መመረቅ ፍትሐዊና ሚዛናዊ የመሠረተ ልማት ዝርጋታን የሚያረጋግጥ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን የገለጹት የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የሀገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውን ይህንን ዘመናዊ አውሮፕላን ማረፊያ በዛሬው ዕለት መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ባደረጉበት ወቅት ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በንግግራቸው ላይ በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ በሁሉም አቅጣጫዎች ትላልቅ አውሮፕላኖችን ማስተናገድ የሚችሉ ወደ 30 የሚጠጉ የአየር ማረፊያዎች እንደሚገኙ ጠቁመዋል። የአየር ማረፊያዎቹ ስርጭት ሀገራዊ አንድነትን እና ልማትን እኩል ለማስፈን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ገልጸው፤በሰሜን 10፣ በምሥራቅ 5፣ በምዕራብ 7 እንዲሁም በደቡብ የሀገሪቱ ክፍል አዲሱን የነገሌ ገዳ አውሮፕላን ማረፊያን ጨምሮ 6 የአየር ማረፊያዎች መኖራቸውን በዝርዝር አብራርተዋል። የቦረና ሕዝብ የኦሮሞን ማንነት፣ባህልና እሴት ጠብቆ ያቆየ እንዲሁም ከጉጂና ባሌ ማኅበረሰቦች ጋር በትብብር የኖረ ታላቅ ሕዝብ መሆኑን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለሰላም ወዳዱ የቦረና እና ጉጂ ሕዝብ ልማት ብንዘገይም ደርሰንለታል ብለዋል። አዲሱ የመሠረተ ልማት አውታር አካባቢው ከአዲስ አበባ ካለው የርቀት ስፋት አንጻር የሚፈጥረውን ተግዳሮት በመቅረፍ፤ ለአካባቢው ማኅበረሰብ ዘርፈ-ብዙ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚኖረው አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የገነባው ይህ አዲስ አውሮፕላን ማረፊያ እንደ ቦይንግ 737 ማክስ ያሉ ዘመናዊና ግዙፍ አውሮፕላኖችን የማስተናገድ ሙሉ አቅም እንዳለውም ተናግረዋል። በሳምንት ሦስት የበረራ ቀናትን የሚያስተናግደው ይህ አየር ማረፊያ፤ የክልሎችን ኢኮኖሚያዊ አቅም ከማነቃቃት ባለፈ የድንበር ተሻጋሪ የንግድ ልውውጥንና የቱሪዝም ዘርፍን ለማሳደግ ታላቅ ራዕይ የሰነቀ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል። የአየር ማረፊያውን ለገነባው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። በቀጣይም ፍትሐዊ ተጠቃሚነትንና የገበያ ትስስርን መሠረት ያደረጉ አዳዲስ የአየር ማረፊያዎች ግንባታ በተለይም በደቡብና ምሥራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች ተጠንተው እንደሚቀጥሉም ጠቁመዋል። ለዚህም ስኬት ሰላም ወዳዱ የጉጂና የቦረና ሕዝብ የጀመረውን የልማት ትብብር አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።
የቦረና ሕዝብ ከተረጅነት ነፃ መውጣቱ በተግባር የታየ ትልቅ ለውጥ ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 162
አዲስ አበባ፤ግንቦት 19 /2018 (ኢዜአ)፦የቦረና ሕዝብ ያሳየው የታታሪነትና የሥራ ወዳድነት መንፈስ የተፈጥሮ ጸጋን ተጠቅሞ ከረሃብ መውጣት እንደሚቻል ትልቅ ማረጋገጫ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ያመለከቱት በምስራቅ ቦረና ዞን ሊበን ወረዳ በሜካናይዜሽን የታገዘውንና በክላስተር እየለማ የሚገኘውን ሰፊ የስንዴ ማሳ በጎበኙበት ወቅት ነው። የአካባቢው ማህበረሰብ ከጥቂት ዓመታት በፊት ይደርስበት ከነበረው ተደጋጋሚ የድርቅ አደጋና የውኃ እጥረት ፈተና ተላቆ፣ በአሁኑ ወቅት በአረንጓዴ ልማት አዲስ ምዕራፍ እየጻፈ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል። ቀደም ሲል እስከ 90 በመቶ የሚደርሰው የዞኑ ነዋሪ በሴፍቲኔት ድጋፍ ይተዳደር እንደነበርና ማህበራዊ ሁነቶች እንኳ ሳይቀሩ በእርዳታ እህል ይከናወኑ እንደነበር ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ዛሬ ላይ ግን ያ የድህነት ታሪክ ተቀይሮ የተረጅነት ምጣኔው ወደ ዜሮ መውረዱን ይፋ አድርገዋል። ይህ በአጭር ጊዜ ውስጥ የተመዘገበውና ማህበረሰቡን ከእርዳታ ጥገኝነት ሙሉ በሙሉ ያላቀቀው ስኬት በቃላት ሊገለጽ የማይችል ተዓምር መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮው አውድማ በሊበን ወረዳ ብቻ 250 ሺህ ሄክታር መሬት በስንዴ ሰብል መሸፈኑን ጠቁመው፤ የተሻሻሉ የውኃ አማራጮችን በመጠቀም ምርታማነቱን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚቻልና ይህም ከአገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ምርትን ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ዕድል እንደሚፈጥር አመላክተዋል። ቀደም ሲል የረድኤት እህል ይከፋፈልበት የነበረው ስፍራ ዛሬ ወደ ሰፊ የምርት ማዕከልነት ተለውጦ ማየት ታላቅ ደስታን የሚፈጥር መሆኑን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህ አይነቱ አመርቂ የልማት ተሞክሮ በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎችም ሊሰፋ እንደሚገባ አሳስበዋል። በርትቶ በመስራት ከልመናና ከረሃብ መውጣት እንደሚቻል የቦረና ሕዝብ በተግባር ማሳየቱንም አክለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማጠቃለያቸው፤ የቦረና ሕዝብ ያሳየው ታታሪነት እና የስራ ወዳድነት መንፈስ የተፈጥሮ ጸጋንና እውቀትን አቀናጅቶ በመጠቀም ረሃብንና ጥገኝነትን ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማስወገድ እንደሚቻል ትልቅ ማረጋገጫ የሰጠ ነው ብለዋል።
በምሥራቅ ቦረና ዞን እየታየ ያለው የግብርና ትራንስፎርሜሽን፤ ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ለመቻል ለምታደርገው ጉዞ ትልቅ ማረጋገጫ ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 27, 2026 212
አዲስ አበባ፤ግንቦት 19/2018 (ኢዜአ)፦በምሥራቅ ቦረና ዞን እየታየ ያለው የግብርና ትራንስፎርሜሽን፤ ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን ለመቻል ለምታደርገው ጉዞ ትልቅ ማረጋገጫ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት፥ በዚህ ወቅት ብቻ ታታሪ አርሶአደሮች ከ176,223 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ላይ እንደሚገኙና ከዚህም ከ3.1 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚያገኙ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል። ይህ የእርሻ ልማት ሥራ ከ101,000 በላይ አባወራዎችንና እማወራዎችን በማሳተፍ እንዲሁም ዘመናዊ ትራክተሮችን በመጠቀም እየተከናወነ እንደሚገኝ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በተደራጀ የክላስተር እርሻ አማካኝነት እምቅ አቅማችንን ወደ ምርታማነት እየቀየርን እንገኛለን ብለዋል። በምሥራቅ ቦረና ዞን ሊበን ወረዳ ከሚገኙት ሰፋፊ የስንዴ ክላስተሮች ጀምሮ እስከ ዋና ዋናዎቹ የጤፍ፣ የበቆሎ እና የቦሎቄ ምርቶች ድረስ እየታዬ ያለው ውጤት፤ የሀገር ውስጥ የምግብ አቅርቦታችንን የማረጋገጥ ጉዞ ላይ ለመገኘታችን ህያው ምስክር መሆኑንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
በክልሉ ሰላምን በማጽናት የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን በቅንጅት ማሳካት ተችሏል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
May 26, 2026 601
ደሴ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ሰላምን በማጽናት የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን በቅንጅት ማሳካት መቻሉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለፁ። በደሴ ከተማ አስተዳደር በ1 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በምረቃው ወቅት እንደገለፁት፤ የክልሉን ሰላም በማጽናት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ሰፋፊ የልማት ፕሮጀክቶችን በመገንባት ለውጤት እንዲበቁ ተደርጓል። የልማት ፕሮጀክቶቹን በቅንጅት በማሳካት የህብረተሰቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በየደረጃው ለመመለስ ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ገልጸዋል። የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ፣ የገበያ መረጋጋትን ለማምጣት፣ የስራ እድልን ለመፍጠር፣ የትምህርትና የጤናው ዘርፍ ተደራሽነትን ለማሳደግ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። የክልሉን እድገት በማረጋገጥ ወደ ሁለተናዊ ብልጽግና የማሸጋገር ተግባራት በቅንጅት እንደሚከናወኑ ጠቁመው በደሴ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር ልማት፣ የአስፋልት መንገድና ሌሎች የመሰረት ልማት ግንባታዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሳሙኤል ሞላልኝ በበኩላቸው የከተማውን ሰላምና ልማት ዘላቂ ለማድረግ ህብረተሰቡን ያሳተፉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዚህም በከተማው የአስፋልት መንገድ፣ የኮሪደር ልማት፣ የመናኸሪያ፣ የፍሳሽ ማስወገጃ፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ፣ የትምህርት ቤት ማስፋፊያና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ተጠናቅቀው ዛሬ ለምርቃ በቅተዋል ብለዋል። የልማት ስራዎቹ መንግስት ለሰው ተኮር ፕሮጀክቶች በሰጠው ትኩረት የተከናወኑ መሆናቸውን ገልጸው የማህበረሰቡን ተጠቃሚነትም አሳድገዋል ነው ያሉት። በምረቃ መርሃ ግብሩ የአማራ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋዬ፣ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)ን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተገኝተዋል።
የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ አስችሎናል - ሸማቾች
May 26, 2026 233
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በየአካባቢው መስፋፋታቸው የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ አስችሎናል ሲሉ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በተለያዩ አካባቢዎች ላይ ሕብረተሰቡ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ በማድረግና ገበያን በማረጋጋት በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑ ይታወቃል። በዚህም የተለያዩ የግብርና ምርቶችን ጨምሮ የተለያዩ ሸቀጦች በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረቡ ይገኛሉ። በጉዳዩ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው አስተያየት ሰጪዎች እንደገለጹት፤ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በአቅራቢያችን በመጀመሩ የግብይት ስርዓቱን ቀልጣፋ እና ምቹ አድርጎታል። አስተያየት ከሰጡ ሸማቾች መካከል ወይዘሮ ገነት አድማሱ፤ ገበያው በአቅራቢያችን በመከፈቱ የፍጆታ እቃዎችን በቀላሉ በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት አስችሎናል ብለዋል። ይህ አይነት ገበያ መኖሩ ለነዋሪዎች ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎትን ከማግኘት ባለፈ የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት ትልቅ አስታዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል። ወይዘሮ ጸጋ አዱሽ በበኩላቸው፤ በቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች የአትክልትና ፍራፍሬ በብዛት ከመቅረቡ ባሻገር ሰፊ አማራጮች የሚገኙበት ነው ብለዋል። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በየአካባቢው መኖሩ ለአቅመ ደካሞችና ረጅም መንገድ ተጉዘው መገበያየት ለማይችሉ ትልቅ ጥቅም እንዳለው ገልጸው፤ ገበያው ላይ በተመጣጣኝ ዋጋ እንደሚያገኝ የገለጸችው ደግሞ ማአዛነሽ መለሰ ናቸው። በቅዳሜ እሁድ ገበያዎች ምርቶቻቸውን ይዘው የቀረቡ ነጋዴዎች በበኩላቸው፤ ጥራቱን የጠበቀ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አስተያየታቸውን ካጋሩን መካከል እየሩሳሌም ሐብቶም፤ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በበርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች ነዋሪዎች ተፈላጊነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል ብለዋል። ይህን ፍላጎት ለማሟላት ጥራት ያላቸውን ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ እያቀረቡ መሆኑን ነው የሚናገሩት። ሌላኛዋ ነጋዴ ቤተልሔም አዱኛ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የዋጋ ንረትን በመቀነስ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማስፋት መጀመሩን ገልጸው፤ ከመደበኛ ሱቆች ከፍተኛ ልዩነት እንዳለው ጠቁመዋል። በአዲስ አበባ ሸማቾች በቀላሉ በአቅራቢያቸው መገብየት የሚያስችሉ በሁሉም አካባቢዎች 250 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች አሉ።
ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማትን ይበልጥ ተወዳዳሪ አድርጓል
May 26, 2026 270
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማትን ይበልጥ ተወዳዳሪ ለማድረግና የህብረተሰብ ተሳትፎን ለማሳደግ ያስቻለ መሆኑን የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ ገለፁ። የካፒታል ገበያ ለሀገሪቱ ኩባንያዎች የረጅም ጊዜ ካፒታል ምንጭ የሚያስገኝና የፋይናንስ አማራጭን በማስፋት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መረጋጋት የሚደግፍ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮ-ቴሌኮም በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ መመዝገቡን ይፋ ያደረገ ሲሆን ይህም ባለአክሲዮኖች በሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ አክስዮናቸውን እንዲያስተዳድሩ፣ እንዲገዙና እንዲሸጡ የሚያስችል ነው። በምዝገባ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ፣ የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጥላሁን እስማኤል (ዶ/ር)፣ የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እንዲሁም የብሔራዊ ባንክና የሌሎች ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ እንደገለጹት፤ ሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ የኢኮኖሚ መዋቅሩን ማዘመን፣ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማሳደግ፣ የመንግሥት ልማት ድርጅቶችን ተወዳዳሪነትና የሕብረተሰቡን ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል ነው። የሀገሪቱ ግዙፍና ስትራቴጂክ ተቋማት ለበርካታ ዓመታት ሙሉ በሙሉ በእጅ ስር እንደነበሩ አስታውሰዋል። የኢኮኖሚ ማሻሻያው ይህን አካሄድ በመቀየር ተቋማቱ ይበልጥ ተወዳዳሪ እንዲሆኑና የህዝብ ተሳትፎ እንዲያድግ በር ከፍቷል ብለዋል። በዚህም ኢትዮ-ቴሌኮም የባለቤትነት ይዞታውን ክፍት በማድረግ የመጀመሪያው የመንግስት የልማት ድርጅት በመሆን በሰነደ ሙዓለ ንዋይ ገበያ በይፋ መመዝገቡን ተናግረዋል። ምዝገባው ለወራት ሲካሄድ የቆየ የዝግጅት ውጤት መሆኑን ጠቅሰው ባለስልጣኑ ሂደቱ ግልፅነትና ዓለምአቀፍ አሰራር የተከተለ እንዲሁም የኢንቨስተሮችን መብት የሚያስጠብቅ እንዲሆን ሲሰራ መቆየቱን አስታውቀዋል። የካፒታል ገበያ መመስረትና ማደግ በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎችን የሀገሪቱ ግዙፍ ድርጅቶች ባለድርሻ የሚያደርግ ነው ብለዋል። የካፒታል ገበያ ለሀገሪቱ ኩባንያዎች የረጅም ጊዜ ካፒታል ምንጭ የሚያስገኝና የፋይናንስ አማራጭን በማስፋት የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መረጋጋት እንደሚደግፍም ተናግረዋል። በሂደት ላይ ያሉ ተቋማትም የድርጅት አስተዳደራቸውን በማሻሻል ወደዚህ መድረክ እንዲመጡና የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ምህዳር ይበልጥ እንዲሰፋና አማራጭ የካፒታል ምንጭ ለማግኘት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለ ነዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ጥላሁን እስማኤል (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮ- ቴሌኮም ወደ ዘመናዊ የሰነደ ሙዓለ ነዋይ ግብይት መግባት ለሥራቸው ታላቅ አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። አያይዘውም ባለአክሲዮኖች ወደ ዘመናዊ የኤሌክትሮኒክስ መገበያያ ሥርዓት መግባታቸውንና የንግድ አካውንት በመክፈት በአገናኝ አማካኝነት መገበያየት እንደሚችሉ ጠቁመዋል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ፤ ኢትዮ-ቴሌኮም የ10 በመቶ ድርሻውን ለዜጎች መሸጡን ተከትሎ የባለአክሲዮኖችን መረጃ የመሰነድና የማደራጀት ሥራ በማከናወን በኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን አጸድቋል ብለዋል። በዚህም አክሲዮን ከገዙ 47ሺህ 377 ባለአክሲዮኖች 10 ነጥብ 7 ሚሊዮን አክሲዮኖችን በመሸጥ 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። ከእነዚህ መካከል የ45 ሺህ ያህሉ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ 10 ነጥብ 1 ሚሊዮን አክሲዮን በ3 ቢሊዮን ብር ለባለ አክሲዮንነት ብቁ ሆነው በመገበያያ ማዕቀፉ መካተታቸውን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት የ96 በመቶ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ የዲጂታል ባለቤትነት ማረጋገጫ ማግኘት መቻላቸውን ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም መድረክ ጠንካራ የተወዳዳሪነት አቅም የገነባ ተቋም ነው - አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ
May 26, 2026 245
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም መድረክ ጠንካራ የተወዳዳሪነት አቅም የገነባ ተቋም መሆኑን በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከቀናት በፊት የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን በተለያዩ ሆነቶች በደማቅ መርሃ ግብር አክብሯል። በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት ተቋማዊ ዕድገትን ማስቀጠል እያስቻሉት ነው። አየር መንገዱ በገነባው የረጅም ዘመናት ዓለምአቀፍ ስምና ዝናም ከአሜሪካ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ኩባንያዎች ጋር ጠንካራ የትብብር አጋርነት እንዳለው ገልጸዋል። ለአብነትም በዓለም አቀፍ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ተፅዕኖ ፈጣሪ ከሆኑት ከቦይንግና ጂኢ-ኤሮስፔስ የአሜሪካ ኩባንያዎች ጋር ጥብቅ አጋርነት ያለው ተቋም መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ዘርፍ አፍሪካን ከቀሪው ዓለም የሚያስተሳስር አስደናቂና ግዙፍ መሰረተ ልማት በማስፋፋት ላይ የምትገኝ ሀገር መሆኗንም አንስተዋል። በዚህም የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአዳዲስ የመንገደኛ አውሮፕላን፣ የበረራ መዳረሻ በማስፋትና በሀገር ውስጥ የአየር ማረፊያ መሠረተ ልማት ግንባታ አስደናቂ ሥራ እየሰራ መሆኑን አብራርተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የገነባው አቅም ቀጣናዊ አየር መንገድ ብቻ ሳይሆን በዓለም መድረክ ላይ ተወዳዳሪ እንዲሆን ማስቻሉን ገልጸዋል። የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅትን ጨምሮ በአስቸጋሪ ወቅቶች በአሜሪካና በኢትዮጵያ አየር መንገድ መካከል የተገነባው ጠንካራ ግንኙነት ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። በኮቪድ ወረርሽኝ ወቅትም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከአሜሪካ ጋር የነበረው ጠንካራ ትብብርና አጋርነት የክትባትና መድኃኒት ቁልፍ ቁሳቁሶችን በማጓጓዝ ከፍተኛ ሚና እንዲወጣ ማስቻሉን አስታውሰዋል። የአየር መንገዱ የወደፊት ዕቅድና የአቅም ግንባታ የትኩረት መስክ ለቀጣይ ስኬቱ ቁልፍ እንደሚሆኑም አምባሳደሩ ጨምረው ገልጸዋል። በዚህም በኢትዮጵያ አየር መንገድ የዕድገት ጉዞ ላይ አሜሪካና የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ኩባንያዎቿ አጋርነታቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በኢትዮጵያና አሜሪካ መካከል ያለው ታሪካዊ ግንኙነት በተለያዩ የልማትና የትብብር መስኮች እየተጠናከረና እያደገ መምጣቱን አስረድተዋል።
በኦሮሚያ ክልል ከተሞች የማህበረሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት ተደርጓል
May 26, 2026 114
መቱ፣ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ከተሞች የነዋሪውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ላይ በትኩረት በመሰራቱ የተሻለ ውጤት መገኘቱ ተገለጸ። በመቱ ከተማ ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 48 የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። በክልሉ ከተሞች የሚከናወኑ የሕንጻዎችና የመሠረተ ልማት ግንባታዎች ምቹ የመኖሪያና ማሕበራዊ አካባቢዎችን ለመፍጠር፣ የመሠረተ ልማት አውታሮችን ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም ቀልጣፋና ዘመናዊ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓትን ለማስፈን ያለሙ መሆናቸውም ተገልጿል። በምረቃ መርሐግብሩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ግርማ ረጋሳ እንደገለጹት፤ በክልሉ ከተሞች በቂ የመሰረተ ልማት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። ፍትሐዊና ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓት ከማስፈንና የማሕበረሰቡን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አንጻር በርካታ ተግባራት መከናወናቸውንም ጠቁመዋል። ኃላፊው አክለውም፣ በክልሉ በየጊዜው እየተገነቡ ለአገልግሎት ክፍት የሚሆኑ የልማት ፕሮጀክቶች ዜጎች የተሻለ ሕይወት እንዲመሩ የሚያስችሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል። የመቱ ከተማ ከንቲባ አቶ ተሻለ ኤጄርሶ በበኩላቸው፣ ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት 48 ፕሮጀክቶች መካከል የትምህርት ቤቶች ግንባታና የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶችን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የመንገድ ዳር የኮሪደር ልማት ስራዎች፣ የንግድ መስሪያ ቦታ ሼዶች፣ የከተማ ግብርና ማዕከላት፣ የኤሌክትሪክ መስመሮች ዝርጋታ እና የከተማ አስተዳደር ሕንጻም መመረቁን ተናግረዋል። ከንቲባው ፕሮጀክቶቹ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ከማዘመንና ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ፣ የሕብረተሰቡን ማሕበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግና ከተማዋን ውብና ምቹ የመኖሪያ አካባቢ ለማድረግ የሚረዱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የመቱ ከተማ ነዋሪዎች መካከል አቶ አብዱራህማን ኢድሪስ እና አቶ ተስፋዬ ኮንቺ ግንባታው ተጠናቆ ወደ አገልግሎት የገባው የከተማ አስተዳደሩ ሕንጻ የከተማዋን ገጽታ የሚያሳድግ ከመሆኑም በላይ፣ ቀልጣፋ፣ ዘመናዊና ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። ወይዘሮ ኑሪያ ሁሴን እና አቶ መሐመድጣሂር አባገሮ በበኩላቸው የተገነቡት ሼዶች የሥራ ዕድል የሚፈጥሩና ሠርተው የሚለወጡበትን ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው ብለዋል። የመንገድ ዳር የኮሪደር ልማቱ የትራፊክ ፍሰቱ የተሳለጠ እንዲሆንና አደጋ እንዲቀንስ ከማድረጉም በላይ፣ የከተማዋን ውበት በመጨመር ለመኖሪያነት ምቹ አድርጓታል ብለዋል።
የከተማውን አገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን ለንግድና ኢንቨስትመንት የበለጠ ምቹ ለማድረግ ትከረት ተሰጥቷል
May 26, 2026 163
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በወላይታ ሶዶ ከተማ የመንግስት አገልግሎትን በማዘመን ከተማውን ለንግድና ኢንቨስትመንት የበለጠ ምቹ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ ። የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር ከ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ለሚያስገነባው የባለ 12 ወለል የቢሮ ሕንፃ ግንባታ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ዛሬ ተካሂዷል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ በወቅቱ እንደገለጹት የወላይታ ሶዶ ከተማ ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ እየሆነች መምጣቷን ተከትሎ አገልግሎት አሰጣጡን ማዘመን አስፈልጓል። ግንባታው የተጀመረው የከተማ አስተዳደሩ የቢሮ ህንጻ ምቹ የሆነ የስራ አካባቢ በመፍጠር የመንግስት አገልግሎት አሰጣጡን ለማዘመን የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል ። የአገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን ከተማዋን ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ ለማድረግ በሚደረገው ሂደት በቅንጅትና በትብብር መስራት አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል። የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማርያም በከተማ አስተዳደሩ ምቹ የስራ አካባቢ ለመፍጠር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የሚገነባው ዘመናዊ የቢሮ ህንፃ የዚሁ አካል መሆኑን ጠቁመው ህንጻው ከተማዋን ለንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭና ተወዳዳሪ ለማድረግ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል፤ የቢሮ ህንጻው በ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር የሚገነባ መሆኑን ጠቁመው ግንባታው በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ አስታውቀዋል ።
ከተማ አስተዳደሩ የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን በልዩ ትኩረት እያከናወነ ነው
May 26, 2026 129
አዳማ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- የአዳማ ከተማ አስተዳደር የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን በልዩ ትኩረት እያከናወነ መሆኑን የከተማው ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ ገለጹ። በአዳማ ከተማ በ17 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ የልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ። የልማት ፕሮጀክቶቹን በዛሬው ዕለት በይፋ የመረቁት የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ኃይሉ ጀልዴ እና የኦሮሚያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ አባቢያ ናቸው። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ አቶ ኃይሉ ጀልዴ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ የቤተሰብ ብልጽግናን፣ የሥራ ዕድል ፈጠራን፣ የገበያ ማረጋጋትንና ማኅበራዊ አገልግሎትን ማዕከል ያደረጉ በርካታ የልማት ሥራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል። በመጀመሪያው የምረቃ ምዕራፍ ዛሬ ከተመረቁት መካከል የመንግስትንና የሕዝብን አቅም በማቀናጀት በ5 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በጀት የተገነቡ 14 የልማት ፕሮጀክቶች ይገኙበታል ብለዋል። እነዚህ ፕሮጀክቶች በትምህርት፣ በጤና፣ በመንገድ መሠረተ ልማት እና በሕዝብ መድኃኒት ቤቶች ላይ ያተኮሩ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ከእነዚህም በተጨማሪ የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ 8 ሺህ ሼዶች በ11 ቢሊዮን ብር ተገንብተው በማኅበር ለተደራጁ ቤተሰቦችና ወጣቶች እየተላለፉ መሆኑን አመልክተዋል። በከተማዋ ኢንዱስትሪ መንደር የተገነቡት እነዚህ ሼዶች ለእንስሳት ማድለብ፣ ለወተት ላም እርባታ፣ ለፍየል ማሞከት፣ ለአሳማና ዶሮ እርባታ እንዲሁም ለሌሎችም ልማቶች አመቺ መሆናቸውን ገልጸዋል። በሼዶቹ አማካኝነት ከ80 ሺህ በላይ በኢንተርፕራይዝ የተደራጁ ወጣቶችና አንቀሳቃሾች ተጠቃሚ መሆናቸውን ከንቲባው አስታውቀዋል። አስተዳደሩ ለሥራ ዕድል ፈጠራ የመሥሪያ ቦታ ከማመቻቸት ባለፈ፣ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ብር የባንክ ብድር እንዲያገኙ በቅንጅት መሥራቱንም ገልጸዋል። ለልማት ፕሮጀክቶቹ ስኬታማነት የከተማው ሕዝብ ላደረገው ከፍተኛ ተሳትፎ ምስጋና ያቀረቡት ከንቲባ ኃይሉ፤ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ሕዝቡ በልማት ሥራዎች ላይ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ አባቢያ በበኩላቸው፤ በመንግስት በጀትና በሕዝብ ተሳትፎ የተገነቡና ሕዝብን ማዕከል ያደረጉ ፕሮጀክቶች፣ የለውጡ መንግስት ለሕዝብ የገባውን ቃል በተግባር የሚያሳይ መሆኑን ማረጋገጫ ናቸው ብለዋል። በአዳማ የተመረቁት ፕሮጀክቶች ለከተማው ማኅበረሰብ ዘርፈ ብዙ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የሚያጎናጽፉ ከመሆናቸውም በላይ፣ የአስተዳደሩን ፕሮጀክቶች ጀምሮ የማጠናቀቅ ግብ በተግባር የሚያሳዩ ሕያው ምስክሮች መሆናቸውን ገልጸዋል። ቀደም ሲል የመሠረተ ድንጋይ የተቀመጠላቸው በርካታ ፕሮጀክቶች እውን ሳይሆኑ የሕዝብ የቅሬታ ምንጭ ሆነው መቆየታቸውን አስታውሰው፤ የለውጡ መንግስት በወሰደው ቁርጠኝነት በርካታ የተጓተቱና አዳዲስ ፕሮጀክቶች በክልሉ ተገንብተው ሕዝቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻላቸውን አብራርተዋል። በዚህ በጀት ዓመትም ለሕዝቡ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መረጋጋት ወሳኝ የሆኑ በርካታ ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን የጠቀሱት ወይዘሮ ሮዛ፤ የተገነቡት ከ21 ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች በየደረጃው የሚገኙ የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን አውስተዋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የክልሉና የከተማዋ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች፣ ነዋሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
በክልሉ አምራች ኢንዱስትሪዎችን በመደገፍ ውጤታማነታቸውን የማረጋገጡ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል
May 26, 2026 121
አርባ ምንጭ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አምራች ኢንዱስትሪዎችን በመደገፍ ውጤታማነታቸውን የማረጋገጡ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ተናገሩ። ርዕሰ መስተዳድሩ ከ75 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባውን የአርባ ምንጭ "ያላ አግሮ ኢንዱስትሪ"ን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በምረቃ መርሃግብሩ ላይ እንዳሉት፤ በክልሉ የልማት ጸጋዎችን ለይቶ እሴት ጨምሮ ለማምረት የኢንዱስትሪ ዘርፉን አቅም ማሳደግ ይገባል። ለዚህም አምራች ኢንዱስትሪዎችን በተለያየ መንገድ በመደገፍ እሴት ጨምረው ለገበያ እንዲያቀርቡና ለአርሶ አደሩም የግብይት አማራጭ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። ዛሬ ወደሥራ የገባው ያላ ወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ክልሉ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ለማበረታታት የሚሰራው ተግባር ውጤታማነት ማሳያ መሆኑንም ተናግረዋል። በክልሉ አምራች ኢንዱስትሪዎችን በመደገፍ ውጤታማነታቸውን የማረጋገጡ ተግባር በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። እንደ አቶ ጥላሁን ገለጻ፤ በክልሉ ኢንዱስትሪዎችን ለመሳብ የተቀናጀ ሥራ ከማከናወኑ ባለፈ የአርሶ አደሩን ምርታማነት የሚያሳድጉ የእንስሳት ዝርያን የማሻሻል፣ የእንስሳት ጤናን የመጠበቅ እንዲሁም የእንስሳት መኖ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። የክልሉ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጥላሁን ብርሃኑ በበኩላቸው፤ በክልሉ ያላ የወተት አግሮ ኢንዱስትሪን ጨምሮ 142 አምራች ኢንተርፕራይዞች አሉ። ኢንዱስትሪ ፓርኮቹ እሴት በመጨመርና ተኪ ምርቶችን በማምረት የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለሚደረገው ጥረት እያገዙ መሆናቸውንም አንስተዋል። ይህን በማጠናከር ለሀገር ዕድገት እና ለዜጎች ተጠቃሚነት የአምራች ኢንዱስትሪ ሚና ለማሳደግ በትኩረት እየተሠራ ነው ሲሉም አክለዋል። የያላ አግሮ ኢንዱስትሪ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ አለማየሁ እስራኤል፤ ኢንዱስትሪው በቀን 24 ሺህ ሊትር ጥራት ያለው ወተት ማቀነባበር እንደሚችል ገልጸዋል። ለ150 ዜጎች ቀጥተኛ የሥራ ዕድል የሚፈጥር ሲሆን፤ በእሴት ሰንሰለት ከ5 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ አስረድተዋል። ኢንዱስትሪው ፓስቸራይዝድ ወተት፣ ተፈጥሯዊ እርጎ፣ ቺዝ፣ ክሬም እና አይብ እንደሚያመርትም ተናግረዋል።
በክልሉ በክረምቱ ወራት ከ3 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሻይ ችግኝ ይለማል
May 26, 2026 121
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው ክረምት ከ3 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሻይ ችግኝ በኩታገጠም እንደሚለማ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የፍራፍሬ ልማት ዳይሬክተር አቶ ቻላቸው አዱኛ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ በክልሉ ከለውጡ ዓመታት ወዲህ ለሻይ ልማት ዘርፍ ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። ክልሉ ምቹ የአየር ንብረት፣ በቂ የዝናብ መጠንና ለሻይ ተክል ተስማሚ የአፈር ዓይነት ያለው በመሆኑ ለዘርፉ ከፍተኛ አቅም እንዳለው ጠቁመዋል። ይህንን ተከትሎም ልማቱ በስፋት እየተከናወነ የሚገኘው የዞኖቹን መልክዓ ምድርና የአየር ንብረት መሰረት በማድረግ ሲሆን፤ በተለይም በጅማ፣ ኢሉአባቦር እና ቡኖ በደሌ ዞኖች ውስጥ በስፋት እየለማ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ በዘንድሮው ዓመት ከተዘጋጀው 120 ሚሊዮን የሻይ ችግኝ ውስጥ፤ 42 ሚሊዮኑን በ3 ሺህ 168 ሄክታር መሬት ላይ በኩታገጠም ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ነው ያሉት። ለዚህም እንዲረዳ የመሬት ልየታ ተካሂዶ በክላስተር የተደራጀ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት የጉድጓድ ቁፋሮ እና የሻይ ችግኝ ተከላ ስራ እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል። ከዘርፉ የሚገኘውን ተጠቃሚነት ለማሳደግም የተሻሻሉ ዝርያዎች የሚባዙባቸው የሻይ ችግኝ ጣቢያዎች በመንግስትና በአርሶ አደሮች ደረጃ ለተከላ ተዘጋጅተዋል ብለዋል። በዘንድሮው የልማት ስራ 1 ሺህ 250 አርሶ አደሮች የሚሳተፉ ሲሆን፤ የሻይ ተክል ችግኞችን በኩታገጠም አሰራር ዘዴ ለመትከል ሙሉ ዝግጅት አድርገዋል ሲሉም አረጋግጠዋል። እስካሁን ባለው ሂደት በክልሉ በአጠቃላይ 2 ሺህ 700 ሄክታር መሬት በሻይ ተክል መሸፈኑን ጠቁመው፤ ከ1 ሺህ 200 በላይ አርሶ አደሮችም እየተሳተፉበት ይገኛል ነው ያሉት። አርሶ አደሩ ለሚያመርተው የሻይ ምርት አስተማማኝ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ታቅዶ በስፋት እየተሰራ እንደሚገኝም ተጠቅሷል። በክልሉ ምዕራብ አካባቢዎች ባለው ከፍተኛ የዝናብ መጠን ምክንያት የመሬት አሲዳማነት ይከሰታል። የሻይ ተክል ደግሞ ይህንን የአፈር አሲዳማነት ተቋቁሞ ከፍተኛ ምርት መስጠት የሚችል በመሆኑ፣ የአካባቢውን ስነ-ምህዳር ለመጠበቅና የአርሶ አደሩን ገቢ ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራበት ሲሉም ተናግረዋል። ይህ የሻይ ልማት አሲዳማ መሬትን የመቋቋም አቅም ያለው በመሆኑ፤ በአሁኑ ወቅት መሰል የአፈር ችግር ባለባቸው በሌሎች የክልሉ አካባቢዎችም ልማቱን ለማስፋፋት ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን አቶ ቻላቸው አዱኛ አስታውቀዋል።
ኢትዮ-ቴሌኮም በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለንዋዮች ገበያ ተመዘገበ
May 26, 2026 199
አዲስ አበባ፤ግንቦት 18/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮ-ቴሌኮም የ10 በመቶ ድርሻ የገዙ ባለአክሲዮኖች ያላቸውን አክሲዮን ማስተዳደር የሚችሉበትና በኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለንዋዮች ገበያ መመዝገቡን ገለጸ፡፡ በምዝገባ መርሃ ግብሩ ላይ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ፣ የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለንዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ጥላሁን እስማኤል፣የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እንዲሁም የብሔራዊ ባንክና የሌሎች ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሃና ተኸልቁ እንደገለጹት፤ ሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ የኢኮኖሚ መዋቅሩን ማዘመን፣ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማሳደግ፣ የመንግሥት ልማት ድርጅቶችን ተወዳዳሪነትና የሕብረተሰቡን ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል ነው። ኢትዮ-ቴሌኮም የባለቤትነት ይዞታውን በከፊል ለሽያጭ ክፍት በማድረግ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል። ይህ ተግባር የፋይናንስ አካታችነትን የሚያሳድግ መሆኑን የጠቆሙት ዋና ዳይሬክተሯ፤ የካፒታል ገበያ መመስረትና ማደግ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎችን የሀገሪቱ ግዙፍ ድርጅቶች ባለድርሻ የሚያደርግ ነው ብለዋል። አክለውም የካፒታል ገበያ የኢኮኖሚ ዕድገት ሞተር በመሆኑ ሁሉም ማኅበረሰብ በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ ሰነደ ሙዓለንዋዮች ገበያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶክተር ጥላሁን እስማኤል በበኩላቸው፤ የኢትዮ- ቴሌኮም ወደ ዘመናዊ የሰነደ ሙዓለንዋይ ግብይት መግባት ለሥራቸው ታላቅ አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። አያይዘውም ባለአክሲዮኖች ወደ ዘመናዊ የኤሌክትሮኒክስ መገበያያ ሥርዓት መግባታቸውንና የንግድ አካውንት በመክፈት በአገናኞች አማካኝነት መገበያየት እንደሚችሉ ጠቁመዋል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ እንዳሉት፤ ኢትዮ-ቴሌኮም የ10 በመቶ ድርሻውን ለዜጎች መሸጡን ተከትሎ የባለአክሲዮኖችን መረጃ የመሰነድና የማደራጀት ሥራ በማከናወን በኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለሥልጣን አጸድቋል። በዚህም አክሲዮን ከገዙ 47 ሺህ 377 ባለአክሲዮኖች 10 ነጥብ 7 ሚሊዮን አክሲዮኖችን በመሸጥ 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። ከእነዚህ መካከል የ45 ሺህ ያህሉ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ 10 ነጥብ 1 ሚሊዮን አክሲዮን በ3 ቢሊዮን ብር ለባለአክሲዮንነት ብቁ ሆነው በመገበያያ ማዕቀፉ ውስጥ መካተታቸውን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት የ96 በመቶ ባለአክሲዮኖች መረጃ ተጣርቶ የዲጂታል ባለቤትነት ማረጋገጫ ማግኘት መቻላቸውን ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ አስታውቀዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ምርጫ
በክልሉ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለምግብነት የሚውሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች በስፋት ተዘጋጅተዋል
May 26, 2026 112
አዳማ፤ ግንቦት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለምግብነት የሚውሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች በስፋት መዘጋጀታቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል ሙዝ፣ አቮካዶ፣ ፓፓያ፣ ብርቱካን፣ ዘይቱን፣ ሎሚ፣ አፕል፣ ማንጎ፣ ግሽጣና ቴምር ይገኙበታል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሙሐመድሳኒ አሚን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደጉ ይገኛሉ። የዚሁ አካል የሆነውን የሙዝ ልማት ይበልጥ ለማሳካትና ምርጥ የሙዝ ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ፣ ባቱን ጨምሮ ከተለያዩ የክልሉ የግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ለአብነትም ባለፉት ዓመታት ከ58 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሙዝ ልማት የተሸፈነ ሲሆን፤ ሥራውን አጠናክሮ ለማስቀጠል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ60 ሚሊዮን በላይ የሙዝ ችግኞች በምርምር ማዕከላትና በአርሶ አደሩ ማሳዎች ላይ እንዲባዙ ተደርጎ ለተከላ ተዘጋጅተዋል ብለዋል። የሙዝ ልማቱን ስኬታማ ለማድረግ ከክረምት ወቅት ባለፈ፤ በተለያዩ የክልሉ ዞኖች የበጋ መስኖ ልማት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ልማቱን በማስፋፋት ረገድ ከዚህ ቀደም የሙዝ ምርት በማይታወቅበት በምሥራቅ ሸዋ ዞንና በሌሎች የክልሉ ቆላማ አካባቢዎች ጭምር በስፋት እየለማ መሆኑን ገልጸዋል። የሙዝ ልማቱ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም ባለፈ፤ አማራጭ የገቢ ምንጭን ለማስፋትና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በመደገፍ ረገድ ወሳኝ ሚና እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። ለፓፓያ ልማትም 100 ሚሊዮን የሚጠጉ ችግኞች የተዘጋጁ ሲሆን፤ እነዚህን ችግኞች ከአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጋር የማስተሳሰር ሥራ ተጀምሯል ነው ያሉት። በተጨማሪም በክልሉ የፍራፍሬ ልማትን ይበልጥ ለማስፋፋት የአቮካዶ፣ የብርቱካን፣ የዘይቱን፣ የሎሚ፣ የአፕል፣ የማንጎ፣ የግሽጣና የቴምር ችግኞችን በጥራት የማዘጋጀት ሥራ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ምክትል ኃላፊው አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያረጋግጡ ውጤታማ እርምጃዎችን እየወሰደች ነው
May 25, 2026 769
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያረጋግጡ ውጤታማ እርምጃዎችን እየወሰደች መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ፍትሐዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በዓለም አቀፍ ማዕቀፍ የዲፕሎማሲ መርህ መሳካት የሚችል የህልውና ጉዳይ መሆኑን አስገንዝበዋል። ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያረጋግጡ ውጤታማ እርምጃዎችን እየወሰደች ትገኛለች። የኢትዮጵያ ፍትሕዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄም ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስርን ለመፍጠር ከምታደርገው ጥረት ጋር ተለይቶ የሚታይ እንዳልሆነ አስረድተዋል። በኢትዮጵያዊያን የጋራ መስዋዕትነት በተገነባው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የሚመነጨውን የኤሌክትሪክ ኃይል ለቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም በአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ስትራቴጂ መነሻነት አህጉራዊ ኢኮኖሚያዊ ውህደትን ለማፋጠን ኢትዮጵያ ፀጋዎቿን በመጠቀም በቁርጠኝነት እንደምትሰራ ነው ያመለከቱት። ኢትዮጵያ ከቀይ ባሕር ጋር ያላትን ቁርኝት ተፈጥሮን ከመልክዓ ምድራዊ ታሪካዊነትን ከሕጋዊነት ያሰናሰለ መሆኑን አስረድተው፤ የባሕር በር ባለቤትነቷን እንድታጣ የተደረገበት በሴራና ተንኮል የተሸረበ አካሄድም የሚያስቆጭና ኢትዮጵያን ደካማ ለማድረግ ካለ እሳቤ የመነጨ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ፀጋዋን በመጠቀም ዕድገትን ካረጋገጠች ስጋታችን ትሆናለች የሚለው ስሌትም የታሪካዊ ጠላቶች ኋላቀርና የተሳሳተ ደምዳሜ ነው ብለዋል። በዚህም የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ታሪካዊ መሠረተ ያለው፣ ተፈጥሯዊና መልክዓ ምድራዊ እውነታ ያለው ሕጋዊና ፍትሐዊነትን አሰናስሎ የያዘ የህልውና ጉዳይ ነው ብለዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ የላቲን አሜሪካ ሀገራት ቦሊቪያና ፔሩ፣ ብራዚልና ፓራጓይ፤ በአፍሪካ የማሊ፣ ሴኔጋልና ኮትዲቯር የተጠቀሙባቸውን የጋራ መፍትሔዎች በተሞክሮነት አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ፍትሐዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በዓለም አቀፍ ማዕቀፍ የዲፕሎማሲ መርህ መሳካት የሚችል የህልውና ጉዳይ መሆኑን አስገንዝበዋል። በዚህም የኢትዮጵያ ታሪካዊ፣ ሕጋዊ፣ መልክዓ ምድራዊና ፍትሕዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ማሳካት እንደሚቻል ተናግረዋል። ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ላላት ሀገር የቅንጦት ሳይሆን የኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነትን የሚያስከብር ቁልፍ የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። ለወደብና ሎጂስቲክስ አገልግሎት በየዓመቱ የምታወጣው ከፍተኛ ሃብት ዓለም አቀፍ የንግድ ተወዳዳሪነትና በጠቅላላው የዕድገት ጉዞ ላይ ትልቅ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩን አስገንዝበዋል።
የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹ የመዝናኛ አማራጭ እየፈጠረ ነው
May 25, 2026 477
አሶሳ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦ የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹ የመዝናኛ አማራጭ እየፈጠረ መሆኑን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን ተናገሩ። ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን የከተማዋ የኮሪደር ልማት አካል የሆነውን የአሶሳ ሲቲ ፓርክን ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። በዚህ ወቅት ርዕሰ መስተዳድሩ እንደገለጹት፤ በአሶሳ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት በርካታ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላት አብረው እንዲገነቡ አድርጓል። ልማቱ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹ የመዝናኛ አማራጭ እየፈጠረ መሆኑንም ተናግረዋል። ለዚህም የኮሪደር ልማቱ በሚከናወንባቸው አካባቢዎች በዘመናዊ መልኩ የተገነቡትን የስፖርት ማዘውተሪያ ቦታዎች፣ የሕጻናት መጨዋቻ እና የመዝናኛ ቦታዎች በማሳያነት ጠቅሰው፤ የልማት ሥራዎቹም ለትውልድ የሚተርፉ ናቸው ብለዋል። አሶሳ ሲቲ ፓርክ ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ከመሆኑ ባለፈ ሕፃናት አዕምሯቸው እንዲታደስ የተለያዩ የመዝናኛ አማራጮችን አካቶ መገንባቱንም ተናግረዋል። የክልሉ መንግስት በሌሎች አካባቢዎችም የኮሪደር ልማቱን ቀጣይነት ባለው መልኩ በማከናወን ለነዋሪዎች ምቹና ጽዱ ከተሞችን ለመፍጠር እየሰራ ይገኛል ብለዋል። የአሶሳ ከተማ ከንቲባ አብዱልከሪም አብዱራሂም በበኩላቸው፤ የአሶሳ ሲቲ ፓርክ የከተማዋን የመዝናኛ ማዕከል እጥረት ችግር የፈታና ለሕፃናትም ልዩ ስጦታ መሆኑ ጠቁመዋል።