ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የበጋ ስንዴ ልማት አመርቂ ውጤት እያስመዘገበ ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 6, 2026 20
አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 28/2018 (ኢዜአ)፦ መሬት ጦም ማደር የለበትም በሚል ጽኑ እምነት የተጀመረው የበጋ ስንዴ ልማት አስደማሚ ውጤት እያስመዘገበ እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዛሬው ዕለት በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ሱሉልታ ወረዳ በ2 ሺህ 150 ሄክታር መሬት ላይ የለማ የስንዴ ማሳን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጉብኝታቸው ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ መንግሥት በግብርናው ዘርፍ በወሰዳቸው ስትራቴጂካዊ እርምጃዎች እየተገኙ ያሉ ውጤቶች አመርቂና ለቀጣይ ሥራዎች ስንቅ የሚሆኑ ናቸው ብለዋል። የበጋ እርሻና የበጋ ስንዴ ልማት በኢትዮጵያ ውስጥ የተለመደ እንዳልነበርም ጠቅላይ ሚኒስትሩ አንስተዋል። መሬት ጦም ማደር የለበትም፤ ከልመና ራሳችንን መገላገል አለብን፤ ሊታረስና ሊለማ የሚችል መሬት መታረስ አለበት በሚል ጽኑ እምነት የበጋ ስንዴ ልማት መጀመሩን አብራርተዋል። የበጋ ስንዴ ልማት ጅማሮው ፈታኝ ቢሆንም፤ አሁን ላይ ሥራው አስደማሚ ውጤት እያስመዘገበ መምጣቱን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከዓመታት በፊት ስንዴን ከውጭ የምታስገባ ብቻ ሳይሆን፤ አነስተኛ ምርት ካላቸው አገራት መካከል ትመደብ እንደነበርም ገልጸዋል። ባለፈው ክረምት 4 ነጥብ 4 ሚሊየን ሄክታር፣ በዘንድሮው በጋ 3 ነጥብ 8 ሚሊየን ሄክታር በድምሩ ከ8 ሚሊየን ሄክታር በላይ መሬት ላይ ስንዴ መታረሱን ገልጸዋል። በአጠቃላይ ከ330 ሚሊየን ኩንታል በላይ የስንዴ ምርት መገኘቱንና ይህም ኢትዮጵያን ስንዴ በማምረት ከአፍሪካ በግንባር ቀደምትነት የሚያስቀምጣት መሆኑን አመልክተዋል። ባለፈው ዓመት ከክረምትና በጋ እርሻ 280 ሚሊየን ኩንታል ስንዴ ምርት መገኘቱን አስታውሰው፤ የዘንድሮው ምርት ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ50 ሚሊየን ኩንታል ብልጫ እንዳለው አብራርተዋል። የተገኘው ከፍተኛ የምርት ልዩነት ከታየባቸው አካባቢዎች አንዱ የሰሜን ሸዋ ዞን መሆኑን ጠቅሰው፤ የማይታረስ መሬት በማረስ በተከናወኑ ተግባራት የስንዴ ምርታማነት ማደጉን ጠቁመዋል። የስንዴ ልማቱ ወንዞችን በመጥለፍና የክረምት ዝናብን በማቆር መከናወኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በቀጣይም ምርታማነትን ለማስፋት በዞኑ በልዩ ትኩረት እንደሚሠራ መረዳታቸውን ተናግረዋል። በሰሜን ሸዋ ዞን አርሶ አደሮች በምርታማነት ማደግ ምክንያት የገቢ አቅማቸው እየጨመረ መምጣቱንም ጠቅሰዋል። የምርታማነትና የገቢ የመሰብሰብ አቅም ማደግ፤ አርሶ አደሮች የተሻለ ኑሮ እንዲመሩ ማድረጉን ም አንስተዋል። የሰሜን ሸዋ ዞን ተሞክሮ በትጋትና ሀብትን በአግባቡ በመጠቀም ትልቅ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል ማሳያ ነው ብለዋል። አሁንም በኢትዮጵያ ስንዴን በማምረትና ቴክኖሎጂን በመጠቀም ከተሠራ፤ ምርታማነቱን በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ እንደሚቻል አስገንዝበዋል። ለዚህ ስኬት አርሶ አደሮች፣ የግብርና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችና አመራሮች በትጋት መሥራት እንዳለባቸውም አሳስበዋል። በግብርናው ዘርፍ የተወሰደው እርምጃ እንደ ሌሎች መስኮች ውጤታማ፣ አመርቂና አዋጭ ሆኖ መገኘቱን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሁን ላይ የማደግ አቅሙ ሰፊ እንደሆነም አንስተዋል። በአጠቃላይ የታየው ሥራ ኢትዮጵያ ትልቅ ተስፋ እንዳላትና የምናልማትን ሀገር ለመፍጠር የሚያስችል መሠረት በሚገባ እየተጣለ መሆኑን የሚያሳይ ነው ብለዋል። ሁሉንም ቀንና ወቅት መጠቀም አለብን፤ ለማምረት፣ ለመሥራትና ለመልፋት፤ ለመብላት ብቻ ሳይሆን ለማብላትና ለመርዳትም ጭምር መጠቀም ይኖርብናል ሲሉም አሳስበዋል። በሥራና በልማት ሂደት የሚገጥሙ ፈተናዎችን በድል እንሻገራለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለዚህም ሁሉም ዜጋ በትጋት እንዲሠራ ጥሪ አቅርበዋል።
በዞኑ ለኩታ ገጠም እርሻና የግብርና ሜካናይዜሽን ትኩረት በመስጠቱ ምርታማነታችንን እያሳደግን ነው
May 6, 2026 18
መቱ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ በኢሉአባቦር ዞን ለኩታ ገጠም እርሻና የግብርና ሜካናይዜሽን ትኩረት በመስጠቱ ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ተናገሩ። የመኸር እርሻ ዝግጅትን አስመልክቶ ኢዜአ ያነጋገራቸው የዞኑ አርሶ አደሮች እንዳሉት የኩታ ገጠም እርሻና የግብርና ሜካናይዜሽንን በመተግበር ምርታማነታቸውን ለማሳደግ ወደ ስራ ገብተዋል። የምርት ማሳደጊያ ግብዓት በወቅቱ በመቅረቡ ማሳቸውን ደጋግመው በማረስና በማለስለስ በዘር ለመሸፈን እየሰሩ መሆናቸውንም ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የዞኑ አርሶ አደሮች መካከል አቶ ገረሙ በዛብህ በመኸር እርሻ በበኩታ ገጠም ለሚያለሙት መሬት የምርት ማሳደጊያ ግብዓት በወቅቱ በመቅረቡ የእርሻ ስራቸውን መጀመራቸውን ተናግረዋል። ዘንድሮ በሰብል ልማት ምርታማነታቸውን ለመሳደግ የግብርና ሜካናይዜሽንና ኩታ ገጠም እርሻን በመጠቀም ለማልማት እየተዘጋጁ መሆናቸውን አንስተዋል። ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በወቅቱ መቅረቡ መሬታቸውን ደጋግመው በማረስ በዘር ለመሸፈን እንዳነሳሳቸው የተናገሩት ደግሞ በአሌ ወረዳ ነዋሪ አቶ ይርጋለም ጫሊ ናቸው። ማሳቸውን በኩታ ገጠም ለማልማት በጋራ እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸው፣ ይህም ምርታማነታቸውን በመጨመር በኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆናቸው ተናግረዋል። በኩታ ገጠም የሚያለሙትን መሬት ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በትራክተር እያረሱ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ አበራ ተስፋዬ ናቸው። ባለፉት ዓመታት ተግባራዊ ያደረጉት ኩታ ገጠም ልማት ኢኮኖሚያ ተጠቃሚነታቸውን ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሳደገው መምጣቱንም ተናግረዋል። በኢሉአባቦር ዞን በመኸር እርሻ 389 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን የገለጹት ደግሞ የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አዳሙ ታከለ ናቸው። በዞኑ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰጠው ትኩረትም በመኸር እርሻ ከሚለማው መሬት 81 በመቶው በኩታ ገጠም እንደሚታረስ ተናግረዋል። በዞኑ የግብርና ሜካናይዜሽን መስፋፋትን ተከትሎ የአርሶ አደሩ በትራክተር የማረስ ልምድ እያደገ መምጣቱን አንስተዋል። በዞኑ በመኽር እርሻ ሩዝ፣ አኩሪ አተር፣ በቆሎ፣ ማሽላና ሌሎች ሰብሎች እንደሚለሙ ገልጸው፣ ለልማቱ የምርት ማሳደጊያ ግብአት በወቅቱ የማድረስ ሥራ እየተጠናቀቀ ነው ብልዋል። በመኸር እርሻው ከ200 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች፣ ማሕበራትና ባለሀብቶችን በማሳተፉ ከ15 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቀዶ ወደ ሥራ መገባቱንም ጠቁመዋል።
በክልሉ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለኢንዱስትሪ ግብዓት፣ ለፍራፍሬና ለቡና ችግኞች ትኩረት ተሰጥቷል
May 6, 2026 36
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን ለሚያረጋግጡ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓት፣ ለፍራፍሬና ለቡና ችግኞች ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ገለጸ። ቢሮው በክልሉ በሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ንቅናቄ ዙሪያ ዛሬ መግለጫ ሰጥቷል። የቢሮው ምክትልና የተፈጥሮ ሃብትና የደን ልማት ዘርፍ ሃላፊ አበባየሁ በየነ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ በክልሉ በየዓመቱ በንቅናቄ የሚመራ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ይከናወናል ብለዋል፡፡ በዚህም በክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን ለሚያረጋግጡ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውሉ፣ ለፍራፍሬና ለቡና ችግኞች ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ለዘንድሮው ተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች 50 በመቶው የፍራፍሬ ችግኝ መሆኑን ጠቅሰው አቮካዶ ቀዳሚ መሆኑንና ፓፓያና ሌሎች ፍራፍሬዎችም እንደሚገኙበት ገልጸዋል። የተያዘውን የቤተሰብ ብልፅግና የማረጋገጥ ዕቅድ ለማሳካት አጋዥ የሆነውን የእንስሳት ሃብት ልማትን ለማሳደግ የእንስሳት መኖ ተከላም ትኩረት እንደተሰጠው አስረድተዋል። በክልሉ ደጋማ አካባቢዎች ያለውን የቀርከሃ ልማት ማስፋፋት የሚያስችሉ የቀርከሃ ችግኞችን በማዘጋጀት ለስራ እድል ፈጠራና ለኢንዱስትሪ ግብዓት ለማዋል መታቀዱን አመልክተዋል። በ416 የመንግስትና የአርሶ አደር ችግኝ ጣቢያዎች ህብረተሰቡን ያሳተፈ የችግኝ ማፍላት ስራ መጠናቀቁን የጠቀሱት ሃላፊው በተከላው ከ27 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት እንደሚሸፈንም ተናግረዋል፡፡ በክልሉ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ልማት የደን ሽፋኑን ከማሳደግ ባለፈ የአፈር ለምነትን በመጠበቅ ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ የተራቆቱ መሬቶች በተከላ መርሃ ግብር እንዲለሙ በማድረግ በእንስሳት እርባታ ለተደራጁ ማህበራት የስራ እድል መፈጠሩንም ጠቁመዋል፡፡
የአዲስ አበባ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል
May 6, 2026 44
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት ማምጣታቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደየፍላጎታቸው ተደራጅተው ለሰለጠኑ ወገኖች የመስሪያ ቦታ አስረክበዋል። በዚሁ ወቅት ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ ከተማ አስተዳደሩ ነዋሪዎችን በፍትሃዊነት የሥራ ዕድል ተጠቃሚ የሚያደርጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   በዚህም ባለፉት የለውጥ ዓመታት የሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረፅ በርካታ ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ በማድረግ ተጨባጭ ውጤት ማምጣት እንደተቻለ ተናግረዋል። በዛሬው ዕለትም በሰው ተኮር ፕሮጀክቶች የተገነቡ በርካታ የመስሪያ ቦታዎችን ለተጠቃሚዎች ማስተላለፍ እንደተቻለ ገልጸዋል። በሁሉም ክፍለ ከተሞች እንደየፍላጎታቸው ተደራጅተው ለሰለጠኑ 1ሺህ 278 ኢንተርፕራይዞችና 3ሺህ 889 አንቀሳቃሾች ሼዶችና የመስሪያ ቦታዎች መተላለፋቸውን አስታውቀዋል። ለሥራ ዕድል ተጠቃሚ ዜጎች የተላለፉ የመስሪያ ቦታዎችና ሼዶችም በአጭር ጊዜ ተገንብተው የተጠናቀቁ መሆናቸውን አንስተዋል።   ሁሉም ዜጋ ተግቶ በመስራትና ድኅነትን በማስቀረት የሀገርን ዘላቂ ዕድገት ማፋጠን እንደሚገባው አስገንዝበዋል። የመስሪያ ቦታ የተሰጣቸው ዜጎችም እራሳቸውን በመለወጥ የስኬት ተምሳሌትነትን በተግባር በማረጋገጥ የኢኮኖሚ ዕድገት አቅም መሆን እንደሚኖርባቸው ጠቁመዋል። በቀጣይም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻን በማልማት የቱሪዝም ማዕከል የማድረጉ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል
May 6, 2026 55
ሀዋሳ፤ ሚያዚያ28/2018(ኢዜአ)፦ የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻን በማልማትና ከአካባቢው መስህቦች ጋር በማስተሳሳር ሀይቁን የቱሪዝም ማዕከል የማድረጉ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የሃዋሳ ከተማ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለጹ። የሀዋሳ ሀይቅ ዳርቻ ልማት የዲዛይን ሥራ ተጠናቅቆ ዛሬ ለህዝብ ይፋ ተደርጓል። ከንቲባው በዚህ ወቅት እንደገለጹት የሀዋሳ ሀይቅ ዳርቻ ልማት ሀይቁን ለትውልድ በሚተርፍ መልኩ አልምቶ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያስችል መሆኑንና ይፋ የተደረገው ዲዛይን በሀይቁ ላይ የሚሰሩ የልማት ሥራዎችን አካቶ የያዘ መሆኑን ተናግረዋል።   ከጥቁር ውሃ እስከ ታቦር ተራራ ድረስ የሚለማውና 12 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው የሀዋሳ ሀይቅ ዳርቻ ልማት ከተማዋን በሀገር አቀፍ ደረጃ ካሉ ከተሞች ጋር ተወዳዳሪና ተመራጭ እንድትሆን ያደርጋታል ብለዋል። ከተማዋ በርካታ የተፈጥሮ ሀብቶች ባለቤት ናት ያሉት ከንቲባው ሀይቁን በአካባቢው ካለው ታቦር ተራራ፣ ፍል ውሀዎች፣ ፏፏቴዎችና ከወንዶ ገነት ጋር በማስተሳሰር አልምቶ የቱሪስት ማዕከል ለማድረግ ይሰራል ነው ያሉት። በሀይቅ ዳርቻ ልማቱ የጥቁር ውሀ አካባቢ፣ በተለምዶ ፍቅር ሀይቅ ተብሎ የሚጠራው የመዝናኛ ስፍራ፣ የሀዋሳ አሳ ገበያ እና አሞራ ገደል አካባቢ ተካትተው አብረው ይለማሉ ብለዋል። የሀይቅ ዳር ልማት ሥራው የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የማማከር አገልግሎት በመስጠት እየሰራ መሆኑም ተጠቁሟል። ዲዛይኑን ይፋ ለማድረግ በተዘጋጀ መርሀ ግብር የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ፣ የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አብርሃም ማርሻሎ፣ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ሀላፊ በየነ በራሳን ጨምሮ ሌሎች የክልሉና የከተማዋ የመንግስት የሥራ ሃላፊዎች እና ባለሀብቶች ተገኝተዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምድር መራቆትና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል በኩል ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው
May 6, 2026 107
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምድር መራቆትና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል በኩል ተጨባጭ ውጤት እያመጣ መሆኑን የኢትዮጵያ ደን ልማት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የቴክኒክ ኮሚቴ ገለጸ። ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት ላለፉት ተከታታይ ዓመታት ያካሄደችው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር፣ በአካባቢ ጥበቃ በኩል ዓለምአቀፍ ትኩረትን የሳበ ለውጥ ማስመዝገብ ችላለች። እስካሁን ከ48 ቢሊየን በላይ ልዩ ልዩ የችግኝ ዓይነቶችን በመትከል የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት አጠናክራ ቀጥላለች። ይህም የደን ሽፋንን በማሳደግ ረገድ ተጨባጭ ውጤት ያመጣ ሲሆን፤ የአፈር መሸርሸርን በመከላከል እና የውኃ ሀብትን በመጠበቅ ለግብርናው ዘርፍ ዕድገት ዓይነተኛ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) በቅርቡ መግለጻቸው ይታወሳል። መርኃ ግብሩ የፍራፍሬ ተከላን በማካተቱ ለምግብ ዋስትና መረጋገጥ እና ለዜጎች ሥርዓተ ምግብ መሻሻል የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተም ይገኛል። የኢትዮጵያ ደን ልማት የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የምድር መራቆትና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል በኩል ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ምርትና ምርታማነትን በተጨባጭ እንዲጨምር ማድረጉን ጠቅሰው ቀደም ሲል በዓመት በሄክታር ይታጠብ የነበረን 130 ቶን አፈር፣ አሁን ወደ 54 ቶን ዝቅ ማለቱንም ገልጸዋል። በተለይም በበጋ ወቅት በሚከናወኑ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራዎች የአፈር መሸርሸርን መከላከልና የውኃ ሀብቶችን መጠበቅ ተችሏል ነው ያሉት። በጥናት እንደተረጋገጠው የምርት እና ምርታማነት ማደጉን፣ የደን ሽፋን መጨመሩንና የአፈር መሸርሸር መቀነሱን የገለጹት አስተባባሪው፤ አረንጓዴ አካባቢዎችን በማስፋፋት ለኑሮ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም ተናግረዋል። ቀደም ሲል ኢትዮጵያ በዓለም የምግብ ድርጅት እጅግ ውስን ፍራፍሬ ከሚያመርቱ ሀገራት መካከል ትመደብ እንደነበር አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ግን ለምግብነትና ለአካባቢ ጥበቃ የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞች ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የችግኝ ጣቢያዎችን በማብዛትና ክትትልን በማጠናከር በመርኃ ግብሩ የሚተከሉ የፍራፍሬ ችግኞች መጠንና ጥራት ላይ ተጨባጭ ለውጦች ተመዝግበዋል ብለዋል። በተለይም በ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞች ዝግጅት በልዩ ትኩረት እየተከናወነ እንደሚገኝም ተናግረዋል። አምና 600 ሚየዮን የሚሆኑ የፍራፍሬ ችግኞች መተከላቸውን አውስተው ዘንድሮ ከዚህ በላይ እንደሚሆን አመልክተዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና አካባቢያዊ ፋይዳዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጎለበቱ መምጣታቸውን ጠቁመው፤ የፍራፍሬ ምርቶችን ለውጭ ገበያ፣ ለአምራች ኢንዱስትሪዎችና ለገበያ ማዕከላት ማቅረብ የጀመሩ አርሶ አደሮች መኖራቸውንም ጠቅሰዋል። እነዚህን መልካም ተሞክሮዎች ይበልጥ ለማስፋት የክትትልና ድጋፍ ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) አረጋግጠዋል። በተጨማሪም የፍራፍሬ ምርቶች ማኅበረሰቡ አማራጭ የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝ በማድረግ ለምግብ ዋስትና መረጋገጥ ጉልህ ሚና እያበረከቱ እንደሚገኙም አብራርተዋል።
በለውጡ ዓመታት የኃይል ማመንጫ መሰረተ ልማቶችን በማስፋፋትና በማዘመን የኤሌክትሪክ ተደራሽነትን ማሻሻል ተችሏል
May 6, 2026 58
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ በለውጡ ዓመታት የኃይል ማመንጫ መሰረተ ልማቶችን በማስፋፋትና በማዘመን የኤሌክትሪክ ተደራሽነትን ማሻሻል መቻሉን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ሞገስ መኮንን ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል እያከናወናቸው ያሉ ሥራዎች በዋናነት በታዳሽ ኃይል (በውኃ፣ በንፋስና በፀሐይ) ላይ ያተኮሩ መሆናቸው፣ ሀገሪቱ ከዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት ጋር የተጣጣመ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት ለያዘችው ስትራቴጂ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። በዚህም የአህጉሪቱ የታዳሽ ኃይል ልማት ማዕከልነቷን ለማረጋገጥ በጀመረችው ጉዞ ያስመዘገበቻቸውን ተጨባጭ ውጤቶች አጠናክራ ቀጥላለች፡፡ ኢትዮጵያ በታዳሽ የኃይል ምንጮች ላይ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም፣ የአፍሪካ ሕብረትን የ2063 አጀንዳ ለማሳካትና አህጉሪቱን በኤሌክትሪክ ኃይል ለማስተሳሰር ቁልፍ ሚና እየተጫወተች ትገኛለች። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ የአይሻ 2 እና የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫዎች በስኬት ተጠናቅቀው ወደ ሥራ በመግባታቸው የሀገሪቱ የኃይል ማምረት አቅም ከ9 ሺህ 752 ሜጋ ዋት በላይ ደርሷል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ሞገስ መኮንን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል፡፡ በኢትዮጵያ ከከተሞች ዕድገት፣ ከኢንዱስትሪዎች መስፋፋት፣ ከዲጂታል ሽግግር ጋር በተያያዘ የኤሌክትሪክ ኃይል ፍላጎት እንዲጨምር ምክንያት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዘመኑ የሚጠይቀውን ኃይል በማቅረብ የዜጎችን ፍላጎት ለማርካት የተጠናከረ የማስፋፊያና የማዘመን ሥራዎችን አከናውኗል ብለዋል፡፡ መንግሥት በለውጡ ዓመታት የተሟላ አገልግሎት ለመስጠት የኃይል ማመንጫ ጣቢያዎችን ማስፋፋትና ማዘመን፣ የኃይል ማስተላለፊያ መስመሮች መገንባት መቻሉን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ 44 በመቶ የነበረው የኃይል ተደራሽነት ሽፋን ባለፉት ሰባት ዓመታት የኃይል መሠረተ ልማቶችን በማስፋፋት ሽፋኑን ወደ 54 በመቶ ማሳደግ ተችሏል ብለዋል፡፡ ከሰባት ዓመት በፊት ኃይል የማመንጨት አቅም 4ሺህ 462 ሜጋ ዋት እንደነበረ በማስታወስ፤ አሁን ወደ 9 ሺህ 752 ከፍ ማድረግ እንደተቻለ ገልጸዋል፡፡ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ከሚያመነጨው የኤሌክትሪክ ኃይል ከፍተኛውን ድርሻ እንደሚይዝ ገልጸው፤ ግድቡ ለሀገራዊ የኃይል ማመንጨት አቅም ዕድገት ገንቢ አስተዋጽኦ አበርክቷል ብለዋል፡፡ ሀገራዊ የኃይል አቅርቦት ፍላጎትን ለመመለስ በተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑን በማንሳት፤ የኢትዮጵያ ፈጣን ዕድገት የሚመጥን የኃይል ተደራሽነትን ለማረጋገጥ ቀሪ ሥራዎች እንዳሉ ገልጸዋል፡፡ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ጣቢያዎችና ማስተላለፊያ መስመሮች ግንባታና ማስፋፊያ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸው፤ በኤሌክትሪክ መሠረተ ልማቶች ላይ የሚፈጸመውን ስርቆት መከላከል ከሁሉም አካላት ይጠበቃል ብለዋል፡፡
በአሪ ዞን በዘንድሮ የበልግ እርሻ ከ51 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ ለምቷል
May 6, 2026 51
ጂንካ፤ ሚያዚያ 28/2018(ኢዜአ):- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አሪ ዞን በዘንድሮ የበልግ እርሻ ከ51 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ በተለያዩ ሰብሎች መልማቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ ጉራልቅ ይዥማልቅ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በበልግ አዝመራው እየለማ ካለው መሬት ውስጥ ከ3 ነጥብ 8 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል ብለዋል። አርሶ አደሩ ከመደበኛው የሰብል ምርት በተጨማሪ የተሻሻሉ የስንዴ፣ የማሽላ እና የበቆሎ ምርጥ ዘሮችን በኩታገጠም በስፋት በማልማት ለሌሎች አካባቢዎች እያቀረቡ መሆኑንም ገልፀዋል። ዞኑ የተለያዩ የአየር ፀባዮች ያለው በመሆኑም በተለይ በደጋው አካባቢ ስንዴ፣ ገብስ፣ ባቄላ እና አተር እየተመረተ መሆኑንም አስታውቀዋል። ወይናደጋ እና ቆላማ በሆኑት አካባቢዎች ደግሞ ጤፍ፣ ማሽላ፣ በቆሎ፣ ሩዝ፣ ለውዝ፣ ሰሊጥ፣ ማሾ እና መሰል ሰብሎች በስፋት እየለማ መሆኑንም አመልክተዋል። በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅሞ ምርታማነቱን እንዲያሻሽል በማሰልጠኛ ማዕከላት ተግባር ተኮር ትምህርት እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል። በዞኑ የባካ ዳውላ አሪ ወረዳ አርሶ አደር ማርቆስ አዲሱ፥ በዘንድሮው የበልግ አዝመራ በቆሎና በአጭር ጊዜ የሚደርሱ የጓሮ አትክልቶችንም በማልማት የገቢ አቅማቸውን ማሳደጋቸውን ነው የሚገልጹት። ሌላው አርሶ አደር ግርማ ከማይ በበኩላቸው፤ በዘንድሮው የበልግ አዝመራ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመጣመር በ10 ሄክታር መሬት ላይ በኩታ ገጠም ስንዴ እያለሙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ከጥቂት ጊዜ ወዲህ የስንዴ ምርት በኢንዱስትሪውም ሆነ በማሕበሩ በስፋት የሚፈለግ በመሆኑ በዘርፉ መስራታቸው ውጤታማ እያደረጋቸው መምጣቱን ጠቁመዋል። ከግብርና ባለሙያዎች የሚሰጧቸውን ምክረ ሀሳቦች በመተግበራቸውም ምርትና ምርታማነታቸውን እንዳሳደገላቸው ነው የተናገሩት።
መንግስት ለተኪ እና ወጪ ምርት የሰጠው ትኩረት ውጤታማ አድርጎናል - አምራች ኢንዱስትሪዎች
May 6, 2026 125
ወልቂጤ፤ ሚያዝያ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አምራች ኢንዱስትሪውን በመደገፍና በማብቃት እንዲሁም ለተኪ እና ወጪ ምርት የተሰጠው ትኩረት ውጤታማ እንዳደረጋቸው በዘርፉ የተሰማሩ አምራቾች ገለፁ። መንግስት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በማምረቻው ዘርፍ ለተሰማሩ ባለሀብቶች የንግድ ከባቢን ምቹ የማድረግ፣ የመሰረተ ልማት አቅርቦት የማሟላትና የፖሊሲ ማሻሻያዎችን የማድረግ ስራዎች በስፋት እያከናወነ ይገኛል። በተጨማሪም ለሀገር ውስጥ አምራቾች ልዩ የድጋፍ ፓኬጆችን በማዘጋጀት አምራቾችን እያበረታታ ነው። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኙ አምራቾች፤ መንግስት አምራች ኢንዱስትሪውን በመደገፍና በማብቃት ለተኪ እና ወጪ ምርት ዕድገት የሰጠው ትኩረት ውጤታማ እንዳደረጋቸው ገልጸዋል። በቡታጀራ ከተማ የሚገኘው የደስታ ጨርቃጨርቅ ፋብሪካ ዋና ስራ አስኪያጁ ያሬድ ወልዴ እንዳሉት፤ ፋብሪካው ለአምራች ኢንዱስትሪው የተመቻቸውን እድል በመጠቀም በዓለም አቀፍ ገበያ ተፈላጊ የሆኑ ምርቶችን እያመረተ ይገኛል። በዚህም ከፍተኛ የሀገር ውስጥ የጥጥ ምርትን በግብዓትነት በመጠቀምና የማምረት ስራውን አጠናክሮ በመቀጠል የአልባሳት ምርቶችን ለአውሮፓ፣ ለአሜሪካና ለተለያዩ የውጭ ሀገራት ገበያዎች እያቀረበ መሆኑን ተናግረዋል። ፋብሪካው ከውጭ ከሚገባው በጥራትና በዋጋ የተሻሉ ምርቶችን በማምረት ለሀገር ውስጥ ገበያም እያቀረበ መሆኑን ነው የሚገልጹት። ከ1 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እያደረገ እንደሆነም አክለዋል። በቡኢ ከተማ የሚገኘው የብሉ ኤሌፋንት ፋይበር ቦርድ ፋብሪካ ኃላፊ ተወካይ ፍቅር ታደሰ በበኩላቸው፤ መንግስት የመስሪያና የመሸጫ ቦታ፣ የብድር ፣ የመሰረተ ልማት አቅርቦቶችን በማመቻቸቱ ውጤታማ እንድንሆን አድርጎናል ብለዋል። አሁን ላይ ፋብሪካው ከውጭ ይገባ የነበረ ለህንፃ፣ ለመንገድ ግንባታና ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ ቦርዶችን ለሀገር ውስጥ ገበያ እያቀረቡ መሆኑን አመልክተው በቀጣይም ምርቱን ወደ ውጭ ለመላክ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በፋብሪካው ስራ ከተፈጠረላቸው ከ600 በላይ ሰዎች በተጨማሪ ለግብዓትነት የሚውሉ የእንጨት ምርቶችን የሚያቀርቡ አርሶ አደሮችንም ተጠቃሚ በማድረግ የተሻለ ህይወት እንዲመሩ እያደረገ መሆኑንም አስረድተዋል። ከውጭ የሚገባውን የፉርኖ ዱቄት በሀገር በመተካት ለማሕበረሰቡ እያቀረቡ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የዳሬም ዱቄት ፋብሪካ ስራ አስኪያጅ ወንድሙ ሀይሌ ናቸው። ፋብሪካው በቀን ከ400 ኩንታል በላይ የስንዴ ዱቄት በማምረት ለገበያ በማቅረብ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ደምሰው ባቾሬ በበኩላቸው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ የኢንዱስትሪውን ዘርፍ በማነቃቃት የማምረት አቅም እንዲያድግ አስችሏል ብለዋል። በእንጨትና ብረታብረት፣ በግብርና ምርቶች ማቀነባበር፣ በልብስ ስፌት እንዲሁም በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪና ወጪ ምርቶችን በጥራትና በብዛት በማምረት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህም ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን በማጎልበት በኩል የድርሻቸውን እየተወጡ ይገኛሉ ብለዋል። ክልሉ በተለያዩ ዘርፎች እምቅ አቅም ያለውና ውጤታማ መሆን የሚቻልበት መሆኑን ገልጸውም በኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሚሰማሩ ባለሃብቶችም ቀልጣፋ አገልግሎት፣ የለማ መሬትና ሌሎች ድጋፎች እንደሚደረጉም አረጋግጠዋል።
የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የአገሪቱን ዘላቂ ዕድገትና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ማዕከል ባደረገ መልኩ እየተገነባ ነው
May 5, 2026 169
አዲስ አበባ፣ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፡-የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ የአገሪቱን ዘላቂ ዕድገትና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ማዕከል ባደረገ መልኩ እየተገነባ መሆኑ ተገለጸ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ካለፈው ሚያዝያ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ግንቦት 30 ቀን ድረስ የሚቆየውን የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ኤክስፖ በይፋ መክፈታቸው ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ በዘንድሮው “ኢትዮጵያ ታምርት” ኤክስፖ ላይ የሀገራዊ ርዕያችንን ተጨባጭ ስኬት መመልከት ትልቅ ክብር ነው ብለዋል። ውጤት ተኮር አመራራችን ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ የኢንዱስትሪ መስፋፋት መንጸባረቁን ጠቅሰው ይኸውም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን አማካይ የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ ባለፉት አራት አመታት ከ2ሺህ 800 በላይ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ በዛሬው ዕለትም "በኢትዮጵያ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የአረንጓዴ ሽግግርን ማፋጠን፤መዋቅራዊ ለውጥን ከአየር ንብረት መቋቋም እና ከንግድ ተወዳዳሪነት ጋር ማጣጣም" በሚል መሪ ሐሳብ ውይይት ተካሂዷል፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ እንደገለጹት፤ በዘርፉ የአረንጓዴ ሽግግርን ለማፋጠንና የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም መዋቅራዊ ለውጥ ለማምጣት በትኩረት እየተሰራ ነው። የኢንዱስትሪ ልማት የኃይል አቅርቦት በታዳሽ ኃይል ላይ የተመሰረተ መሆኑ ትልቅ ዕድል መሆኑን ጠቅሰው፥ ምርቶች ሲመረቱ የአፈር፣ የውሃ፣ የአየርና የድምጽ ብክለት እንዳያስከትሉ ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ ለሀገር የኢኮኖሚ ምሰሶ እንደመሆኑ መጠን፣ ከተፈጥሮና አካባቢ ጥበቃ ጋር ተስማምቶ መጓዝ ይገባዋል ብለዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል የመወያያ ጽሑፍ ያቀረቡት ተባባሪ ፕሮፌሰር ታደለ ፈረደ በበኩላቸው፥ ኢትዮጵያ የዘላቂ ልማት ግቦችን መሠረት አድርጋ እየሠራች መሆኑን ጠቁመዋል። በኢትዮጵያ የተገነቡት ኢንዱስትሪ ፓርኮች ታዳሽ ኃይልን የሚጠቀሙ በመሆናቸው፣ ከብክለት የጸዳ ምርት እንዲመረትና ለአየር ንብረት የማይበገር የኢኮኖሚ ግንባታ ትልቅ መሠረት እንዲጣል አስችሏል ብለዋል። ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማኔጅመንት ትምህርት ክፍል የተሳተፉት ኢትዮጵያ ለገሰ (ዶ/ር) በበኩላቸው ኢትዮጵያ በታዳሽ ኃይል ላይ የምታደርገው ጥረት በቀጣይ የአረንጓዴ ማኑፋክቸሪንግ ማዕከል እንድትሆን ያስችላታል ብለዋል። ምርቶቹ በታዳሽ ኃይል መመረታቸው በርካታ ፋይዳዎች እንደሚስገኝ ጠቅሰው በዋናነት በዓለም ገበያ ላይ ለሥነ-ምህዳር ተስማሚ የሆኑ ምርቶች ያላቸው ተፈላጊነት እየጨመረ በመሆኑ ኢትዮጵያ ተጠቃሚ ትሆናለች ብለዋል። በተጨማሪም ከአፍሪካ አልፎ ወደ ተለያዩ የዓለም ገበያዎች በስፋት ለመግባትና ተወዳዳሪ ለመሆን እንደሚያግዝ ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የኮሪደርና የቱሪስት መዳረሻ ልማት ስራዎች ከተሞችን ለኑሮ ምቹ ከማድረግ ባለፈ ዘርፈ ብዙ ዕድሎችን አምጥተዋል
May 5, 2026 202
ሀዋሳ ፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ በከተሞች እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደርና የቱሪስት መዳረሻ ልማት ስራዎች ከተሞችን ለኑሮ ምቹ ከማድረግ ባለፈ ዘርፈ ብዙ ዕድሎችን ይዘው መምጣታቸውን ምሁራን ገለጹ። "በኢትዮጵያ ዘመናዊ ቱሪዝም ልማት ውስጥ ፈጠራና ዘላቂነት" በሚል መሪ ሀሳብ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮጵያ ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 15ኛው ሀገር አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስና የኮሪደር ልማት የልምድ ልውውጥ መድረክ መካሄዱ ይታወሳል። በወቅቱም ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት ምሁራን እንደገለጹት፤ የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ በመቀየር ውብና ማራኪ ከማድረግ ባለፈ የቱሪስት ቆይታን በማራዘም ዘርፈ ብዙ ዕድሎችን ይዞ መጥቷል። በኢትዮጵያ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደርና የመዳረሻ ልማት ስራዎች የቱሪስትን ቆይታ ከማራዘም ባለፈ ለከተማ ነዋሪው ምቹ የመዝናኛ አማራጭ ይዞ መምጣቱን ነው ምሁራኑ የተናገሩት። በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስትራቴጂ ፕሮግራሞች ማኔጅመንት ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኢንጂነር እሸታየሁ ክንፉ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ከተሞች ያላቸውን ጸጋ ለይተው የሚያለሟቸው የመዳረሻ ልማት ስራዎች በርካታ ጠቀሜታዎችን ይዘው መጥተዋል። በመላ ሀገሪቱ ከተሞችን ለማዘመንና ምቹ የመኖሪያ፣ የስራና የቱሪስት ማዕከል ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደርና የመዳረሻ ልማት ስራዎች ለነዋሪው ምቹ የመዝናኛ አማራጭና ጎብኚዎች ቆይታቸውን እንዲያራዝሙ ለማድረግ አስችሏል ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢኒሼቲቭ አዲስ አበባ ላይ የተከናወኑ የኮሪደርና የመዳረሻ ስፍራዎች ልማት ለዚህ ማሳያ መሆናቸውን ጠቅሰው ይህም የከተማዋን ተመራጭነት በማሳደግ ለገቢ ማደግም የበኩሉን ሚና እየተጫወተ ይገኛል ነው ያሉት። በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዚዳንት ታፈሰ ማቲዮስ (ዶ/ር)፤ በሀዋሳ ከኮሪደር ልማት ስራው በተጓዳኝ የሀይቅ ዳርቻ ልማት ስራውን ዩኒቨርሲቲው በአማካሪነት እያገዘ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የሀይቅ ዳርቻ ልማቱ ደረጃውን የጠበቀ በአካባቢው ያለውን የተፈጥሮ ሀብት ባማከለ መልኩ የሚሰራ በመሆኑ ከተማዋን በአዲስ ገጽታ፣ አዲስ ምዕራፍ ውስጥ እንደከተታት ተናግረዋል። በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ተባባሪ ፕሮፌሰር ምህረት ደናንቶ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የከተሞችን ውበት የጨመረው የኮሪደር ልማት ስራ የመዝናኛና የገቢ ማግኛም ጭምር ዕድልን ይዞ መምጣቱን ተናግረዋል። የከተማዋ ግርማ ሞገስ የሆነው የሀዋሳ ሀይቅን በተገቢው ለመጠቀም የተጀመረው የሀይቅ ዳርቻ ልማት ስራ ተመራጭነቷን በማሳደግ ለዕድገቷ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ነው ያሉት። የኮሪደርና የመዳረሻ ልማቱ ለቱሪዝም እድገቱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ያመለከቱት ደግሞ በቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት የከልነሪ አርት ከፍተኛ ኢንስትራክተር አቶ ጌትሽ ገደፋው ናቸው። መንግስት የቱሪዝም ዘርፍ እንዲያንሰራራ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራት ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
በልዩ ኢኮኖሚ ዞኖች የ19 ቢሊዮን ብር ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ ቀርቧል
May 5, 2026 238
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦በልዩ ኢኮኖሚ ዞኖች አማካኝነት በዘጠኝ ወራት ውስጥ 19 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያለው ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ መቅረቡን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን አስታወቀ፡፡ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የአምስት ቢሊዮን ብር ብልጫ የታየበት ሲሆን፣ የተካሄደው ሪፎርምና መንግሥት ያደረገው ድጋፍ ውጤት መሆኑም ተጠቁሟል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል የተዘጋጀውን አራተኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ በከፈቱበት ወቅት እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ የኢንዱስትሪ ዘርፉ እያደገ መጥቷል። የኢንዱስትሪ ዘርፉ ዕድገት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ሲጀመር ከነበረበት 4.7 በመቶ አሁን ላይ ወደ 10.7 በመቶ መድረሱን በወቅቱ ገልጸዋል። ባለፉት አራት ዓመታትም ከውጭ ይገባ የነበረን የ14.5 ቢሊዮን ዶላር ምርት በሀገር ውስጥ መተካት እንደተቻለም ነው የገለጹት።   የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፍጹም ከተማ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ የሚገቡ ኢንቨስተሮች ምርታቸውን 100 በመቶ ለውጭ ገበያ እንዲያቀርቡ የሚገደዱበት አሠራር ነበር። ሆኖም መንግሥት ባደረገው ሪፎርም አምራቾች ምርታቸውን 50 በመቶ ለውጭ፣ 50 በመቶ ደግሞ ለአገር ውስጥ ገበያ እንዲያቀርቡ መፈቀዱን አስታውቀዋል። ይህ አዲስ አቅጣጫ የውጭ ምንዛሬን ከማስገኘት ባለፈ፣ ወደ አገር ውስጥ የሚገቡ ምርቶችን በአገር ውስጥ ምርት ለመተካት (Import Substitution) ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ብቻ ኮርፖሬሽኑ ከሚያስተዳድራቸው ልዩ ኢኮኖሚ ዞኖች የ19 ቢሊዮን ብር ምርት ለአገር ውስጥ ገበያ መቅረብ መቻሉን አመልክተዋል። አሁን የተገኘው ውጤት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ከዓምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከፍተኛ የሆነ ልዩነት ያለው ምርት ለአገር ውስጥ እያቀረቡ መሆኑን እንደሚያሳይ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በርካታ ፋብሪካዎች በግንባታና በማሽን ተከላ ሥራ ላይ የተሰማሩ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ እነዚህ ፋብሪካዎች በቅርቡ ወደ ምርት ሲገቡ የአገር ውስጥ ምርት አቅርቦት በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያድግም አንስተዋል።   መንግሥት ያካሄደው ሪፎርምና ኮርፖሬሽኑ ባደረገው ልዩ ድጋፍና ማበረታቻ የተገኘው ውጤት በቀጣይ ዓመታት ይበልጥ እንዲጨምር በትኩረት እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። ኮርፖሬሽኑ የኢንቨስትመንት መዳረሻዎችን በማስፋፋትና ለአምራቾች ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር፣ የአገሪቷን ኢኮኖሚ ለመደገፍ የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።
የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት በሥራ ዕድልና በቴክኖሎጂ ሽግግር ተጠቃሚ አድርጎናል
May 5, 2026 247
ሐረር፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት፤ ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም ባለፈ የቴክኖሎጂ ሽግግርና ክህሎታቸውን በማሳደግ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው የእድሉ ተጠቃሚዎች ገለጹ። የሐረሪ ክልል በታሪኩና በቱሪስት መስህብነቱ ቢታወቅም፣ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የክልሉን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት በኢንዱስትሪ ልማት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል። በተለይም መንግስት የኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት ለማሳደግና የውጭ ምንዛሬን ለማዳን የጀመረው "ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ በክልሉ ውጤት ማምጣት ጀምሯል። ክልሉ ለኢንቨስትመንት አመቺ የሆኑ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎችን በማጠናከር፣ አዳዲስ ፋብሪካዎች ወደ ሥራ እንዲገቡና ነባሮቹ ደግሞ በሙሉ አቅማቸው እንዲያመርቱ እያደረገ ያለው ጥረት ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ፣ የኢንዱስትሪ ባህልና የቴክኖሎጂ ዕውቀት በአካባቢው እንዲሰርጽ እያደረገ ይገኛል።   ወጣት ፈርሃን ተውፊቅ የሐረር ከተማ ተወላጅ ሲሆን በከተማው ኢንዱስትሪ ዞን በሚገኘው ማስ ኢንጅነሪንግ ኢንተርፕራይዝ በተለያዩ የሙያ ዘርፍ እርሱና ሌሎች ጓደኞቹ የስራ እድል እንደተፈጠረላቸው ተናግሯል። በክልሉ የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት የተሻለ የቴክኖሎጂ ክህሎት እንዲያገኙ ከማስቻሉ ባለፈ ከውጭ የሚመጡ ምርቶችን በኢንተርፕራይዙ በማምረት የውጭ ምንዛሬን የማስቀረት ተግባር እያከናወኑ መሆኑን አስረድቷል። በከተማው በብረታብረት ዘርፍ ወደ ስራ በመግባት ከኢንዳስትሪው ባገኙት የስራ እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ነስረዲን አህመድ ናቸው። በተለይም የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት ለከተማዋ የኮሪደር ልማት የሚውሉ የፖል ብረት ምርቶች በስፋት እንዲቀርቡና ከተማዋን እንዲያስውቡ ማድረጉን አቶ ነስረዲን ገልጸዋል። በዱቄት ፋብሪካ የስራ ዕድል ተጠቃሚ በመሆኗ እራሷንና ቤተሰቧን እያገዘች መሆኑን የገለጸችው ደግሞ ወጣት ኤደን ፍሰሃ ናት። በሐረር የኢንዱስትሪዎች መነቃቃት ለስራ ፈላጊውም ጭምር አስተዋፅኦ እያደረገ መሆኑን ተናግራለች። ከዚህ ባለፈም ልምድ፣ ተሞክሮና የተሻሻሉ አሰራሮችን እየቀሰሙ እንደሚገኙ የገለጸችው ወጣት ኤደን፣ በዚህም ለፋብሪካ ባለቤቶች ምስጋና አቅርባለች።   ፋብሪካው 120 ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ፈጥሯል ያሉት ደግሞ በከተማው ኢንዱስትሪ ዞን የሚገኘው የቀነኒ ዱቄት ፋብሪካ ስራ አስኪያጅ አቶ ተስፋ አስፋው ናቸው። ፋብሪካው በአሁኑ ወቅት ከውጪ ይገባ የነበረውን የስንዴ ዱቄት በአገር ውስጥ በማምረት እና ለአካባቢው በማከፋፈል ላይ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይም የፓስታ፣ መኮሮኒን እና ሌሎች ምርቶችን ለማምረት የዝግጅት ስራ እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። የሐረሪ ክልል ኢንተርፕራይዞች ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ሃላፊ አቶ ኡስማኢል ዩስፍ በበኩላቸው፤ በክልሉ አዳዲስና ነባር መካከለኛና ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎችን ወደ ስራ በማስገባት ተኪ ምርቶችን በስፋት የማምረት ተግባር መጠናከሩን ተናግረዋል።   በተለይም የክልሉን ኢኮኖሚ ይበልጥ የሚያጎለብቱና የስራ እድልን የሚያስፋፉ ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች ግንባታቸው ተጠናቆ ማሽነሪዎችን የማስገባት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን አሲዳማ አፈርን በኖራ በማከም ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
May 5, 2026 100
ደብረ ማርቆስ ፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን አሲዳማ አፈርን በኖራ በማከም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ሃላፊ አቶ ጥላሁን ንጋቱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በመጪው መኸር ምርትና ምርታማነትን በሁሉም አማራጭ በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል ርብርብ እየተደረገ ነው።   በዚህም ከ46 ሺህ ሄክታር በላይ በአሲድ የተጠቃ መሬትን በኖራ በማከም ቀድሞ ወደ ነበረበት ምርታማነት ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በኖራ አቅርቦት ዙሪያ ከአቅራቢ ድርጅቶች ጋር በመነጋገር በፍጥነት ለአርሶ አደሩ ለማድረስ እየተሰራ መሆኑን የገለጹ ሲሆን እስካሁን ከ3ሺህ ኩንታል በላይ ኖራ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ተናግረዋል። በቀጣይ ወራትም አስፈላጊውን መጠን ኖራ በማቅረብ አሲዳማ የሆነውን አፈር የማከሙ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። በመኸር ምርቱ የታቀደውን የምርት ጭማሪ ለማስመዝገብም መሬትን በኖራ ከማከም ባሻገር አዳዲስ አሰራሮችንና ቴክኖሎጂዎችን መጠቀም ላይ በማተኮር እየተሰራ ነው ብለዋል።   በዞኑ የማቻከል ወረዳ የቅዳማን ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ባየልኝ ሙላት እንደገለጹት በአሲድ የተጠቃውን አንድ ሄክታር ማሳቸውን በኖራ በማከም ዘር እየዘሩ ነው። በኖራ አክመው ከሚዘሩት ሰብል ከአምስት ኩንታል በላይ የምርት ጭማሪ እንዳገኙ ጠቁመው ያገኙትን ጥቅም ለማሳደግም ዘንድሮ ከ30 ኩንታል በላይ ኖራ ማሳቸው ላይ መበተናቸውን ተናግረዋል። በአነደድ ወረዳ የጉዳለማ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ጊዜአለው አግደውም ማሳቸውን በኖራ በማከም ለምነቱ እንዲመለስ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። አሁን ላይም ከግማሽ ሄክታር በላይ ማሳቸው ላይ ኖራ በመበተን ደጋግመው ማረሳቸውን ጠቁመው በቀጣይም ከዘሩ ጋር ቀላቅለው በመዝራት ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እንደሚሰሩም አመልክተዋል። በመጪው የመኸር ምርት ከ660 ሺህ ሄክታር በላይ መሬትን በተለያዩ ሰብሎች በማልማት ከ26 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱ ተመልክቷል።
በክልሉ የቡና ኢንሼቲቭ ግቦችን ለማሳካት የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን የማስፋት ሥራ በትኩረት እየተከናወነ ነው
May 5, 2026 164
አዳማ ፣ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ተግባራዊ እየተደረገ ያለውን የቡና ኢንሼቲቭ ግቦችን ለማሳካት፤ የተሻለ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችን የማስፋት ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ሙሐመድሳኒ አሚን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ የቡና ምርታማነትን ለመጨመር የተሻለ ምርት የሚሰጡ ችግኞች ለአርሶ አደሩ በስፋት ተደራሽ እየሆኑ ይገኛሉ። የቡና ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ አንዱ የትኩረት አቅጣጫችን በምርምር የተሻሻሉ የቡና ዝሪያዎችን ለአርሶአደሩ በስፋት ተደራሽ ማድረግ ነው ብለዋል። በክልሉ ለዘንድሮው የቡና ልማት በቂ የቡና ችግኞች ተዘጋጅተዋል ያሉት የቢሮው ምክትል ሃላፊ፤ በአሁኑ ወቅት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የክልሉ ዞኖችና ወረዳዎች የችግኞቹ ተከላ እየተከናወነ ይገኛል ነው ያሉት። በዘንድሮው የቡና ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለመሸፈን ታቅዶ ርብርብ እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። ምርትና ምርታማነትን ለማረጋገጥ የችግኝ ተከላው በሳይንሳዊ ዘዴ እንዲመራ እየተደረገ መሆኑን የገለጹት ምክትል ኃላፊው፤ ለዘርፉ ባለሙያዎችና ለአርሶ አደሮች አስፈላጊው ስልጠና መሰጠቱንም ጠቁመዋል። ምርት የማይሰጡና ያረጁ የቡና ዛፎችን የመንቀልና የተሻለ ምርት በሚሰጡ በአዲስ ዝሪያ የመተካት ስራ ከማከናወን ባለፈ የጉንደላ ስራም በስፋት መከናወኑን ተናግረዋል። በእስካሁኑ ሂደት ያረጀና ተገቢውን ምርት የማይሰጥ ቡና በመንቀል በ66ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተሻለ ምርት የሚሰጡ የቡና ችግኞች መተከላቸውን ተናግረዋል። በተመሳሳይ ባረጀ የቡና ጉንደላ ስራ ከ120ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ያለውን ተክል መሸፈን መቻሉንም ጨምረው ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የቡና ችግኞችን በስፋት ለመትከል የሚያስችል አስተማማኝ የዝናብ ሁኔታ መኖሩን የገለጹት አቶ ሙሐመድሳኒ፤ አርሶ አደሩ በሙሉ አቅሙ ተከላውን በማከናወን ጊዜውን በአግባቡ እንዲጠቀም ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ በዘንድሮው ዓመት 16 ሚሊዮን ኩንታል የቡና ምርት መሰብሰቡን የገለፁት አቶ ሙሐመሳኒ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 251 ሺህ ቶን ቡና ለማዕከላዊ ገበያ መቅረቡንም ጨምረው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሀገር ውስጥ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን እያሳደገ ነው
May 4, 2026 146
አዲስ አበባ ፤ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሀገር ውስጥ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን እያሳደገ እንደሚገኝ ከፍተኛ የዘርፉ ምሁራንና ተመራማሪዎች ገለጹ። በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል እየተካሄደ የሚገኘው አራተኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ዛሬም ቀጥሎ ውሏል። በሁለተኛ ቀን ውሎው በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር፣ በሰው ኃይል ልማትና በምርታማነት አቅም ዙሪያ ያተኮረ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሲለሺ ለማ፤ ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ዕድገትን የሚያፋጥን ጠንካራ መሰረት እየጣለች ነው ብለዋል።   የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ጠንካራ መሰረቶችም ምርታማነትና የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማፋጠን ዓለም አቀፍ የተወዳዳሪ አቅም እየገነባ መሆኑን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ምርቶቿንም በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት የትግበራ ሂደት ቀጣናዊ የንግድ ትስስርን አዳዲስ ዕድሎችን እየፈጠረች እንደምትገኝ ተናግረዋል።   በተባበሩት መንግስታት የንግድና ልማት ጉባኤ (UNCTAD) የምርታማነት አቅምና ዘላቂ ልማት የአፍሪካ ዲቪዥን ኃላፊ ሙሴ ደለለኝ (ዶ/ር)፤ ኢንዱስትሪ ምርታማነት የዕድገት መሰረት ነው ብለዋል። በዚህም ኢትዮጵያ የፈጠረችውን የኢንቨስትመንት አስቻይ ምኅዳር የበለጠ በማስፋት ዕድገትን የሚያፋጥን የኢንዱስትሪ ምርታማነት ማጠናከር እንደሚጠበቅባት አስገንዝበዋል። በኢትዮጵያ የልማት ምርምር ኢንስቲትዩት የድህነት ቅነሳና ዘርፈ-ብዙ ጥናት ተመራማሪ አለበል ባይራው (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር የዕድገት ማሳለጫ መሳሪያ ነው ብለዋል። በዚህ በኩል ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን በማሳደግ ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የውጭ ምንዛሬ ወጪን ማስቀረት በሚያስችል ወሳኝ ምዕራፍ እያለፈች መሆኗን ገልጸዋል።   በዓለም አቀፍ የዕድገት ማዕከል የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ ቴዎድሮስ መኮንን (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለኢንዱስትሪ ምርታማነት አቅም የሆነ የሰው ሃይል ያላት ሀገር ናት ብለዋል። የኢትዮጵያ አብዛኛው ህዝብ በወጣት የዕድሜ ክልል የሚገኝ በመሆኑም የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማፋጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል።
በሀረሪ ክልል ለቱሪዝም ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አበረታች ውጤት የታየበት ነው
May 4, 2026 109
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ በሀረሪ ክልል ለቱሪዝም ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አበረታች ውጤት የተመዘገበበት ነው ሲሉ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ገለጹ። በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር የተመራው የአስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች የልዑካን ቡድን በሀረር ኢኮ ፓርክ የጅብ ትርኢትን ተመልክተዋል።   ከንቲባው በጉብኝታቸው ላይ እንደተናገሩት በክልሉ መሰል የቱሪዝም መስህቦችን ለማስፋፋት የተደረገው ጥረት አበረታች ውጤት የታየበት ነው። በክልሉ የተገነባው የጅብ ትርዒት ማሳያ ፓርክም ለቱሪስቶች ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ያሉት ከንቲባው ይህም የቱሪዝም ዘርፉን በማጎልበት ከተማዋን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ የሚያደርግ መሆኑን ገልፀዋል።   የሀረር ከተማን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎችም ውጤታማና አበረታች መሆናቸውን እንደተመለከቱ ገልጸዋል። በጉብኝቱ ላይ የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪን ጨምሮ የሀረሪ ክልል እና የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ውጤቶችን በማስፋት የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት ማፋጠን ያስፈልጋል
May 4, 2026 111
አዲስ አበባ፣ሚያዚያ 26/2018 (ኢዜአ)፦በሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የተገኙ ውጤቶችን በማስፋት የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት ማፋጠን እንደሚያስፈልግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የገንዘብ ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማትን የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርት ገምግሟል።   የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በሪፖርታቸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በዘንድሮው በጀት ዓመት 10 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት ማስመዝገብ የሚያስችል ስኬት እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር በተሰራው ሥራም በታኅሳስ 2018 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ የዋጋ ግሽበቱን ዘጠኝ ነጥብ ሰባት በመቶ በማድረስ ወደ አንድ አሃዝ ማውረድ መቻሉን አመልክተው፤ የመጋቢት ወርም ወደ ዘጠኝ ነጥብ አራት በመቶ መውረዱን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት መንግስት ከብሔራዊ ባንክ ምንም ዓይነት ብድር አልወሰደም ያሉት ሚኒስትሩ፤ ከብሔራዊ ባንክ ቀጥታ የሚወሰደው ብድር እንዲቆም መደረጉም የዋጋ ንረትን እንዲቀንስ አድርጓል ብለዋል። በቡድን 20 የጋራ ማዕቀፍ አማካኝነት ኢትዮጵያ የዕዳ ሽግሽግ እፎይታ እንድታገኝ ስኬታማ የሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ ድርድር መደረጉን ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብሩ በጥብቅ የፊስካል ፖሊሲ ቁጥጥርና የቁጠባ ዲሲፕሊን በመመራቱ ኢትዮጵያን ከአፍሪካ ቀዳሚ ዕድገት የምታስመዘግብ ሀገር እያደረጋት መሆኑን አንስተዋል። የምክር ቤቱ አባላትም፤ የሚኒስቴሩን የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርት መነሻ በማድረግ በዋጋ ግሽበት፣ የዕዳ ሽግሽግና ተያያዥ የኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ ጥያቄና አስተያየት አቅርበዋል። የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በምላሻቸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የሚያስከትለውን ጫና ለመቀነስ በደመወዝ ጭማሪ፣ ማዳበሪያ፣ ነዳጅ፣ የምግብ ዘይትና መሰረታዊ ሸቀጦች ላይ መንግስት ድጎማ እያደረገ ነው ብለዋል። በሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ በተደረጉ ስኬታማ ድርድሮችም ኢትዮጵያ ከጣሊያንና ፈረንሳይ ጋር የዕዳ ሽግሽግ ስምምነት መፈረሟን አስረድተዋል። ከቻይና ጋርም የዕዳ ሽግሽግ ስምምነት መፈረም የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው ያሉት የገንዘብ ሚኒስትሩ፤ ከዩሮ ቦንድ አበዳሪዎች ኮሚቴ ጋር ያለው ድርድር መቀጠሉን ገልጸዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ደሳለኝ ወዳጄ፤ ሪፖርቱ ቀጣይነት ያለው ዕድገት መኖሩን የሚያሳይ ነው ብለዋል። በቀጣይም በዋጋ ንረትን፣ ዕዳ ሽግሽግ፣ በወጪና ገቢ ንግድ አፈፃጸም የተገኙ ውጤቶችን በማጠናከር የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙን ውጤቶችን በማስፋት ዕድገትን ማስቀጠል እንደሚገባ አሳስበዋል።
ኮርፖሬሽኑ በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ወደ ተግባር ምዕራፍ ተሸጋግሯል 
May 4, 2026 141
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ ኮርፖሬሽኑ ባስቀመጠው ራዕይ መሠረት በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ከፍተኛ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቶ አሁን ላይ ወደ ተግባር ምዕራፍ መሸጋገሩን የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ረሻድ ከማል ገለጹ። የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን ጁባ ከተማ በቤት ግንባታ ዘርፍ መሰማራት የሚያስችለውን ታሪካዊ ስምምነት ተፈራርሟል። በሁለቱ ሀገራት መካከል በመሪዎች ደረጃ የጋራ የልማት ትብብር በሚፈልጉ ጉዳዮች ላይ አብሮ ለመስራት ስምምነት መደረሱን ተከትሎ በኮርፖሬሽኑ እና በደቡብ ሱዳን ማዕከላዊ ኢኳቶሪያል ግዛት መካከከል በቤት ልማት ላይ በጋራ መስራት የሚያስችል ስምምነት ተፈጽሟል፡፡   በኢትዮጵያ ፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን እና በደቡብ ሱዳን የማዕከላዊ ኢኳቶሪያል ግዛት መንግሥት መካከል የተደረገው ይህ የመግባቢያ ሰነድ፣ በጁባ ከተማ በቤቶች ልማትና አስተዳደር ዘርፎች በጋራ መሥራት የሚያስችል መሠረት ጥሏል ነው ያለው ኮርፖሬሽኑ። ስምምነቱን የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) እና የማዕከላዊ ኢኳቶሪያ ግዛት መንግሥት አስተዳዳሪ ኢማኑኤል አዲል በይፋ መፈረማቸውን ኢዜአ ከኮርፖሬሽኑ ያገኘው መረጃ ያመላክታል። ይህ ውል ኮርፖሬሽኑ ያለውን የረጅም ጊዜ ልምድና የቴክኒክ አቅም በመጠቀም በጁባ ከተማ ዘመናዊ የመኖሪያ ቤቶች፣ የንግድ ሕንፃዎችና የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ግንባታ እንዲያከናውን ሰፊ መንገድ እንደሚከፍትም ተመላክቷል። ዋና ሥራ አስፈጻሚው በሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደተናገሩት፣ ኮርፖሬሽኑ ባስቀመጠው ራዕይ መሠረት በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ከፍተኛ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቶ አሁን ላይ ወደ ተግባር ምዕራፍ ተሸጋግሯል።   ኮርፖሬሽኑ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ያላቸውና አዋጭ በሆኑ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል። በደቡብ ሱዳን የማዕከላዊ ኢኳቶሪያ ግዛት መንግሥት አስተዳዳሪ ኢማኑኤል አዲል በበኩላቸው፣ በኢትዮጵያ እየተመዘገበ ያለው ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና ፈጣን የከተሞች ለውጥ ለመላው አፍሪካውያን ተምሳሌት መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታም በርካታ የልማት ሥራዎችን ተዘዋውረው መመልከታቸውን ተናግረዋል። በተለይም በቤት ልማት ዘርፍ በኢትዮጵያ ያለውን ተሞክሮ ከኮርፖሬሽኑ ጋር በመሆን በጁባ ከተማና በግዛቱ ተግባራዊ ለማድረግ እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል።   ስምምነቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ትስስር ከማጠናከር ባሻገር፣ ኮርፖሬሽኑ በቤት አስተዳደርና ልማት ያለውን ውጤታማ ተሞክሮ ለግዛቱ ባለሙያዎች የሚያጋራበትንና የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን የሚሰጥበትን ዕድል ያመቻቻል ብለዋል። የስምምነቱን አፈጻጸም በቅርበት የሚከታተል፣ ዝርዝር የፕሮጀክት ሰነዶችን የሚያዘጋጅና አጋዥ የመፍትሔ ሐሳቦችን የሚያመነጭ የጋራ ቴክኒክ ኮሚቴ እንዲቋቋም መወሰኑም ተመላክቷል። ይህ ስምምነት የሁለቱ ሀገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ከማሸጋገሩ በላይ፣ የኢትዮጵያን የቤቶች ልማት ተሞክሮ ወደ ጎረቤት ሀገራት ለማስፋፋት ትልቅ መነቃቃትን እንደሚፈጥርም ተገልጿል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም