ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በዞኑ የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የማሳደግ ተግባራት ተጠናክረው ቀጥለዋል
Mar 6, 2026 15
ደብረ ማርቆስ ፤ የካቲት 27/2018(ኢዜአ)፦በምስራቅ ጎጃም ዞን የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የማሳደግ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን የዞኑ እንስሳትና ዓሳ ሃብት መምሪያ አስታወቀ። በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከእጣንና ሙጫ ምርት ሽያጭ ከ280 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለማግኘት ትኩረት ተደርጓል የመምሪያው ኃላፊ አቶ ዳኘ ዋሴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ተግባራዊ መደረጉ የእንስሳት ልማቱን በግብዓትና በአዳዲስ አሰራር ለማገዝ አስችሏል። በበጀት ዓመቱ ሰባት ወራትም ከ33 ሺህ በላይ በሚሆኑ ላሞች ላይ የዝርያ ማሻሻል ተግባር መከናወን መቻሉን ጠቁመው በዚህም አርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። ዝርያ የማሻሻል ስራው በኮርማ፣ በተፈጥሮ ድሪና በሆርሞን መሆኑን ጠቁመው በማዳቀል ስራው ከ17 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። ዝርያ የማሻሻል ስራ መከናወኑ ከነባር ላም በቀን ይገኝ የነበረውን አንድ ነጥብ ስምንት ሊትር ወተት ከ10 ሊትር በላይ ለማሳደግ ማስቻሉን ጠቁመዋል። የስጋ ምርታማነትን ከማሳደግ አንፃርም በተከናወኑት ተግባራት እስከ 30 ኪሎ ግራም ጭማሪ ምርት ማግኘት እንደተቻለም አስረድተዋል። በበጀት ዓመቱ የተከናወነው የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ስራ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ40 በመቶ በላይ ብልጫ እንዳለውም ተገልጿል። አፈጻጸሙ ባለሙያዎች ቀበሌ ድረስ ወርደው በመስራታቸው የመጣ ውጤት ነው ብለዋል። ከተጠቃሚዎች መካከል የማቻከል ወረዳ የውላ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ገነቱ ገላጋይ እንዳሉት ፤በሁለት ላሞቻቸው ላይ በተካሔደው ዝርያ የማሻሻል ስራ በቀን ከ20 ሊትር በላይ ወተት እያገኙ ነው። ያገኙትን ጥቅም ይበልጥ ለማሳደግም በዚህ ዓመት ሁለት ላሞችን በኮርማ ማዳቀላቸውን ተናግረዋል። በዚሁ ወረዳ የአማሪ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር ዘላለም ሲሳይ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል ዝርያዋን ካሻሻሏት አንዲት ላም እስከ 12 ሊትር ወተት በቀን በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን አንስተዋል። በዘንድሮ ዓመትም በሶስት ጊደሮች ላይ የዝርሻ ማሻሻል ስራ መስራታቸውን ነው የገለጹት። የወተት ምርት ለማህበራት በማስረከብ የምግብ ፍጆታቸውን ከመሸፈን አልፎ ተቀማጭ ገንዘብ እንዲኖራቸው ማድረጉን ተናግረዋል። በዞኑ እስከ 200 ሺህ የሚደርሱ ዝርያቸው የተሻሻሉ እንስሳት እንደሚገኙ ከመምሪያው የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
ፕሮጀክቱ የከተማችን ብቻ ሳይሆን የሀገራችን ኩራትና ገጽታን የሚቀይር ስኬት ነው -ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Mar 6, 2026 35
አዲስ አበባ፤ የካቲት 27/2018(ኢዜአ)፦ከኡራኤል - ቦሌ መድኃኔዓለም እስከ ቦሌ ቪአይፒ (VIP) ተርሚናል የሚያገናኘው የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት የከተማችን ብቻ ሳይሆን የሀገራችን ኩራትና ገጽታን የሚቀይር ስኬት ሆኗል ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ ከንቲባዋ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፤ ከኡራኤል - ቦሌ መድኃኔዓለም እስከ ቦሌ ቪአይፒ (VIP) ተርሚናል የሚያገናኘው የኮሪደር ልማት፣ ዘርፈ-ብዙ ሥራዎችን አካቶ መጠናቀቁን አስታውቀዋል፡፡ ከንቲባዋ፤ የከተማችን ተጨማሪ ድምቀት በሆነው ከኡራኤል - ቦሌ መድኃኔዓለም እስከ ቦሌ ቪአይፒ (VIP) ተርሚናል የሚያገናኘውን የኮሪደር ልማት፣ ለአካባቢው ተጨማሪ ውበት የሚያጎናፅፉ እና ለሕዝብ ከፍተኛ ጥቅም ያላቸውን ዘርፈ-ብዙ ሥራዎች አካትተን አጠናቀናል ሲሉ ገልጸዋል። ይህ መስመር ቀደም ሲል ደረጃቸውን ያልጠበቁ የአስፋልት መንገዶች፣ የእግረኛ መንገድ እጥረት፣ የሳይክል መንገድ አለመኖር እና ከፍተኛ የመኪና ማቆሚያ(ፓርኪንግ) ችግር የነበረበት እንደነበር አስታውሰዋል። በተጨማሪም ምንም ዓይነት የስፖርት ሜዳዎችም ሆኑ የሕፃናት መጫወቻዎች ያልነበሩበት፣ የህንፃዎች ውበት በቆሻሻና ዕድሳት በማጣት እንዲሁም አላስፈላጊ በሆኑ ተለጣፊ ግንባታዎች ተሸፍኖ የቆየ እንደነበርም ገልጸዋል። ዛሬ ግን ለኮሪደር ልማቱ ምስጋና ይግባውና አካባቢው ለአይን ማራኪና ዘመናዊ መልክ ይዟል ብለዋል። ፕሮጀክቱ የሚከተሉትን ዋና ዋና ስራዎች አካትቷል፦ • 5.3 ኪ.ሜ የአስፋልት መንገድ፦ 60 ሜትር ስፋት ያለውና በሁለቱም በኩል 4 መስመሮችን የያዘ፤ • የትራንስፖርት ተርሚናል፦ ዘመናዊ የታክሲና የአውቶቡስ ተርሚናሎች፤ • የእግረኛና የሳይክል መንገድ፦ 10.538 ኪ.ሜ የእግረኛ መንገድ (ከ5 እስከ 10 ሜትር ስፋት ያለው) እና 4 ኪ.ሜ የብስክሌት መስመር፤ • የመኪና ማቆሚያ፦ በመንግሥትና በግለሰቦች ትብብር በአንድ ጊዜ እስከ 2,000 መኪናዎችን(900 ከቤት ውጭ እና 1,100 በህንፃዎች ውስጥ) ማቆም የሚችሉ ስፍራዎች፤ • የኤሌክትሪክ ቻርጅ ጣቢያ፦ 3,442.38 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ የተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ፤ • የትራንስፖርት መቆሚያዎች፦ 15 የታክሲና አውቶቡስ ማቆሚያዎች፤ • የንግድና መዝናኛ ስፍራዎች፦ 8 ካፌዎች ከሕዝብ መጸዳጃ ጋር፣ ፕላዛዎች እና ለአነስተኛ ንግዶች የሥራ ዕድል የፈጠሩ ሱቆች፤ • አረንጓዴ ልማት፦ 5 ፋውንቴኖችን ያካተቱ ውብ አረንጓዴ ስፍራዎች፤ • የስፖርት ማዘውተሪያዎች፦ የእግር ኳስና የቅርጫት ኳስ ሜዳዎች እንዲሁም የሕፃናት መጫወቻ ስፍራዎች፤ • የህንፃዎች ዕድሳት፦ ውበታቸው ተመልሶ የታደሱ ከ200 በላይ ሕንፃዎች ፣ በከፍተኛ ጥራትና ፍጥነት ተሰርተዋል። እነዚህን ሁሉ አስደናቂ ተግባራት ሦስት ወራት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ አጠናቅቀን ለሕዝብ አገልግሎት ክፍት በማድረጋችን ታላቅ ደስታ ይሰማናል ያሉት ከንቲባዋ ይህ ፕሮጀክት የከተማችን ብቻ ሳይሆን የሀገራችን ኩራትና ገጽታን የሚቀይር ስኬት ሆኗል ነው ያሉት። ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ የንግድ እንቅስቃሴውን በእጅጉ አነቃቅቷል፤ ወደፊትም የተሻለ ውጤት እንደምናገኝበት ሙሉ እምነት አለን ብለዋል። ከእኛ ጋር በመሆን በትጋት የደከማችሁ አመራሮች፣ ሠራተኞችና ባለሙያዎች፣ በ24/7 የሥራ ባሕል ቀንና ሌሊት የለፋችሁ ሁሉ ምስጋና ይገባችኋል ሲሉም ምስጋና አቅርበዋል። እንዲሁም በመስመሩ ላይ ያላችሁ ባለሀብቶች፣ ነጋዴዎች፣ የቤትና የሕንፃ ባለቤቶች ሌት ተቀን ከጎናችን በመቆም ላደረጋችሁት ከፍ ያለ ትብብርና ማበረታቻ ምስጋናችን የላቀ ነው ብለዋል።
በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ውስጥ ባለሀብቶችን በቀጥታ ማሳተፍ የሚያስችል ዘመናዊ የገበያ ስርዓት ተፈጥሯል
Mar 5, 2026 113
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ እድገት ውስጥ ባለሀብቶችን በማንኛውም ጊዜና ቦታ በቀጥታ ለማሳተፍ የሚያስችል ዘመናዊ የገበያ ስርዓት መፈጠሩን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ሥራ አስፈጸሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) ገለፁ። የኢትዮጵያ የሰነደ መዋዕለ ንዋይ ገበያ “ንዋይ” የተሰኘ የሞባይል መተግበሪያን ይፋ አደረገ የኢትዮጵያ የሰነደ መዋዕለ ንዋይ ገበያ (ESX) የካፒታል ገበያን ለሁሉም ዜጎች ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል “ንዋይ” የተሰኘ የሞባይል ግብይት መተግበሪያ ዛሬ ይፋ አድርጓል። ይህ መተግበሪያ በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ማንኛውም ግለሰብ በእጁ ላይ ያለውን የሞባይል ስልክ በመጠቀም፣ በአክሲዮን እና የዕዳ ሰነዶች ግብይት ውስጥ በቀጥታ ለመሳተፍ የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ሥራ አስፈጸሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) በመተግበሪያው የምረቃ ስነ-ስርዓት ላይ እንደተናገሩት፣ መተግበሪያው ሁሉም ዜጋ በአቅሙ ልክ የሚሳተፍበትን ምቹ እና ዘመናዊ የገበያ ዕድል ፈጥሯል። ባለፉት ጥቂት ዓመታት ወደ ሥራ የገቡት የቴሌ ብር እና የሲቢኢ (CBE) መተግበሪያዎች ያስመዘገቡት ስኬት ለዚህ መተግበሪያ ውጤታማነት እንደ ማሳያ እንደሚጠቀስም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የሰነደ መዋዕለ ንዋይ ገበያ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ጥላሁን እስማኤል (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ አዲሱ መተግበሪያ ገበያውን በእያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ እጅ ተደራሽ ያደርገዋል። በሀገሪቱ የኢኮኖሚ እድገት ውስጥ ባለሀብቶችም በማንኛውም ጊዜና ቦታ በቀጥታ እንዲሳተፉ እድል እንደሚፈጥርም ገልጸዋል። በተጨማሪም መተግበሪያው የሰነድ ግዢና ሽያጭ ትዕዛዞችን በስልክ ማስተላለፍና መፈጸም እንደሚያስችል ተናግረዋል። በቀጣይ ኢንቨስተሮች ለገበያው ያላቸውን ልምድ እንዲያዳብሩ የአገናኝ አካላት ጥረት ወሳኝ መሆኑን አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሀና ተህልቁ በበኩላቸው፤ በርካታ ሀገራት ወደዚህ ዓይነት የቴክኖሎጂ ሥርዓት ለመድረስ ረጅም ጊዜ እንደወሰደባቸው አስታውሰዋል። ኢትዮጵያ ግን ካለፈው ተሞክሮ በመማር በአጭር ጊዜ ውስጥ ዘመናዊ የገበያ ሥርዓት ማበጀቷን ገልጸዋል። ለዚህም ስኬት መንግስት ህጎችን ግልፅና ተገማች ማድረጉ እንዲሁም ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠሩ ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን ጠቁመዋል። ይህን የገበያ ሥርዓት ልዩ የሚያደርገው አካታችነቱ በመሆኑ፣ በሁሉም የሀገሪቱ ጫፍ ያሉ ዜጎች ተሳታፊ እንዲሆኑና የኢንቨስትመንት አካውንት በመክፈት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ግንዛቤ መፍጠር እንደሚገባ አሳስበዋል። መተግበሪያው በአሁኑ ወቅት በአንድሮይድ (Android) እና በአይኦኤስ (iOS) ስልኮች ላይ ለመጫን ዝግጁ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ ይህም ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ የካፒታል ገበያ ባለቤት ለማድረግ በሚደረገው ጉዞ ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑ ተመልክቷል።
በክልሉ የሚገኙ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማት ከዘርፉ የሚገኝን ገቢ ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
Mar 5, 2026 105
ዱራሜ ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኙ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማት ከዘርፉ የሚገኝን ገቢ ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ፡፡ ጊቤ ሸለቆ ብሔራዊ ፓርክን የሚጎበኙ ቱሪስቶች ቁጥር እየጨመረ መጥቷል ርዕሰ መስተዳድሩ በከምባታ ዞን በሀምበሪቾ የቱሪዝም መዳረሻ ስፍራ ለሚገነባው "የኢትዮጵያውያን መንደር ፕሮጀክት" ግንባታ ማስጀመሪያ የመሰረተ ድንጋይ አኑረዋል፡፡ ፕሮጀክቱ የአድዋ አርበኞች ሀውልትን፣ 30 ጎጆዎችን፣ የህፃናት መጫወቻና መማሪያ ክፍሎችን፣ የመሰብሰቢያ አዳራሽን ጨምሮ ሌሎች የተለያዩ መዝናኛዎችን ያካተተ ሆኖ ግንባታው እንደሚከናወንም ተጠቁሟል፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በክልሉ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማት ከዘርፉ የሚገኝን ገቢ ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል፡፡ ቀደምት አባቶች ነፃነቷን አስጠብቀው ባቆዩልን ሀገር አዳዲስ ፕሮጀክቶችን እውን በማድረግ ለተተኪው ትውልድ ማስተላለፍ የወቅቱ ትውልድ ኃላፊነት ነው ሲሉም ተናግረዋል፡፡ የ"ሀምበሪቾ የኢትዮጵያውያን መንደር ፕሮጀክት" ሁሉንም ዜጎች የሚያሰባስብ ከመሆኑም በተጨማሪ የቱሪዝም ዘርፉን በማነቃቃት ረገድ ከክልል አልፎ ለሀገር ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ስለመሆኑ አመልክተዋል፡፡ በክልሉ የጢያ ትክል ድንጋይ የቱሪስት መዳረሻን ጨምሮ የሀምበሪቾ የኢትዮጵያውያን መንደርን በታቀደለት ጊዜ አጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ለማድረግ የክልሉ መንግስት ተገቢውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ገልጸዋል፡፡ የከምባታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አረጋ እሸቱ በበኩላቸው የ"ሀምበሪቾ የኢትዮጵያውያን መንደር ፕሮጀክት" በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተጀመረ የልማት ስራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የሀምበሪቾ ኢኮ ቱሪዝም መዳረሻ በጎብኚዎች ዘንድ ያለው ተፈላጊነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱንም ጠቁመዋል፡፡ የቱሪስት መዳረሻውን በሚመጥን መልኩ በህብረተሰቡ ተሳትፎ በትብብር ለማልማት የሀብት ማሰባሰብ ስራ ስለመጀመሩም አስረድተዋል፡፡ በዚህም የኢትዮጵያውያን መንደር ፕሮጀክቱን የክልሎችና የሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች ህዝቦችን ባህል፣ ታሪክና እሴት በሚገልጽ መልኩ እንደሚለማ ገልጸዋል፡፡ ለፕሮጀክቱ እውን መሆን አስተዳደሩና የአካባቢው ማህበረሰብ የሚጠበቅበትን እንደሚወጣም አረጋግጠዋል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ የክልልና የዞኑ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችን ጨምሮ የአካባቢው ተወላጆችና የንግዱ ማህበረሰብ አካላት ተሳትፈዋል፡፡
በአፋር ክልል በመስኖ ልማት እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት አበረታች ናቸው - ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)
Mar 5, 2026 115
ሰመራ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል በመስኖ ልማት ላይ እየተሰሩ ያሉ ስራዎች አበረታች መሆናቸውን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስትሩ በክልሉ እየተከናወኑ ያሉ የመስኖ ልማት ስራዎችን ፤ግድብና የእንስሳት መኖ ልማት ስራን ተመልክተዋል። ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) በጉብኝታቸው ወቅት እንደገለጹት፤ በአፋር ክልል የመስኖ ስራዎችን በማጠናከር ረገድ የሚከናወኑ ተግባራት የሚበረታቱ ናቸው። በተለይም በዱብቲ ወረዳ በማህበር ተደራጅተው በፍራፍሬና አትክልት ልማት የተሰማሩ ወጣቶች እያከናወኑት ያለው ስራ ውጤታማ መሆኑን ገልጸዋል። የዱብቲ ወረዳ የቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ሙባረክ መሐመድ፣ በወረዳው በሁለት ማህበር የተደራጁ ወጣቶች ወደ ስራ ገብተዋል ብለዋል። ማህበራቱ በ14 ሄክታር መሬት ላይ ፓፓያ፣ ሙዝ፣ ማንጎ፣ ብርቱካን፣ ሎሚና ቴምር በማልማት ላይ መሆናቸውን አብራርተዋል። የመስኖ ስራዎችን በማጠናከር ወጣቶች ወደ ስራ እንዲገቡ ከማድረግ አኳያ በሚኒስቴሩ ስር የሚገኘው የቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። የቆላማ አካባቢ ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት በአፋር ክልል በ5 ክላስተርና በ23 ወረዳዎች ላይ የተለያዩ የልማት ስራዎችን በማከናወን፣ ለአርብቶ አደሩ ኑሮ መሻሻል ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑም ተመልክቷል። በጉብኝት መርሃ ግብሩ ላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ የአፋር ክልል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል።
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ያደረጋቸው የሕግና የአሠራር ማሻሻያዎች ውጤት አስገኝተዋል
Mar 5, 2026 80
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ በፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ባለፉት የለውጥ ዓመታት ሥራዎቹን በውጤታማነት ማከናወን የሚያስችሉ የሕግና የአሠራር ማሻሻያዎች መደረጋቸውን ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ ገለጹ፡፡ "የዳኝነትና ዴሞክራሲ ተቋማት እመርታ፤ ለተሳካ ሀገረ መንግሥት ግንባታ!" በሚል መሪ ሀሳብ በዳኝነትና ዴሞክራሲ ተቋማት ቅንጅት ላይ የሚያተኩር ሀገራዊ መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። በፍርድ ቤቶች የዳኝነት ነፃነትን ያጠናከሩ እና የፍትሕ ሥርዓቱን ማዘመን ያስቻሉ ስኬታማ ተግባራት ተከናውነዋል መድረኩ በዋናነት በሀገሪቱ የፍትህ ሥርዓት እና በዴሞክራሲ ግንባታ ሂደት ውስጥ ቁልፍ ሚና ያላቸው ተቋማት ካለፉት ዓመታት ተሞክሮ በመነሳት በቀጣይ ጠንካራ የሀገረ መንግሥት ግንባታ በሚያረጋግጡባቸው ጉዳዮች ላይ በዝርዝር መክሯል፡፡ የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ ባቀረቡት የመነሻ ጽሑፍ፤ ተቋሙን ከወገንተኝነት የጸዳ፣ ነፃና ገለልተኛ ለማድረግ ሰፊ የሕግና የአሠራር ማሻሻያዎች መደረጋቸውን ገልጸዋል። ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ተቋሙን ነፃ የሚያደርጉ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች በሕግ ደረጃ መሟላታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የኦዲት ሽፋን ዕድገት በተመለከተም የፋይናንሻል ኦዲት ሽፋን መቶ በመቶ መከናወኑን ጠቅሰው የክዋኔ ኦዲት ደግሞ ከነበረበት 24 በመቶ ወደ 41 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ ከአካባቢያዊ ኦዲት እስከ መረጃ ሥርዓትና ልዩ ኦዲት ድረስ አዳዲስ ዘርፎች ተደራጅተው ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመዋል። በተከናወኑ የለውጥ ሥራዎች የተቋሙ ተዓማኒነትና ጥራት መጨመሩን ጠቁመው በኦዲት ግኝቶች አማካኝነት በርካታ ገንዘቦችን ተመላሽ እንዲሆን ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ይህም ተቋሙ የሀገርን ሀብት በማስጠበቅ ረገድ ያለውን ሚና በተግባር ያረጋገጠ መሆኑ ተመላክቷል። ተቋሙ የቴክኖሎጂ ለውጡን ተከትሎ ሥራዎቹን ይበልጥ ለማዘመን በርካታ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ጠቁመው የኦዲት አስተዳደርና የመረጃ ትንተና ሥርዓቶችን ወደ ዲጂታል ለመቀየር እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እንዲሁም የባለሙያዎችን አቅም በቀጣይነት ለመገንባት ራሱን የቻለ የሙያ ማበልጸጊያ ኢንስቲትዩት የማቋቋም ግብ እንዳለውም ጠቁመዋል።
የባቡር መስመር ዝርጋታው የሀገር በቀል የግንባታ አቅማችንን በተግባር ያሳየንበት ነው
Mar 5, 2026 249
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦የኤ.ኤ.ም.ጂ ኢንዱስትሪ ፓርክ የባቡር መስመር ዝርጋታ የሀገር በቀል የግንባታ አቅማችንን በተግባር ያሳየንበት ነው ሲሉ በግንባታው የተሳተፉ ባለሙያዎች ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ በባቡር መሰረተ ልማት ዘርፍ የነበራትን የውጭ ድጋፍ ፍላጎት በሀገር በቀል እውቀትና ክህሎት በከፍተኛ ደረጃ እየተካች ትገኛለች። ሀዋሳ ከተማን ምቹ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው - ከንቲባ ጥራቱ በየነ ለዚህም ማሳያ የሚሆነው በሀገር ውስጥ ባለሙያዎች እየተገነባ ያለውና የኤ ኤም ጂ (AMG) ኢንዱስትሪ ፓርክን ከዋናው መስመር ጋር የሚያገናኘው የባቡር ፕሮጀክት በአሁኑ ወቅት መጠናቀቂያው ላይ ደርሷል። ይህ ስኬት ሀገሪቱ በዘርፉ ያላትን ቴክኒካዊ ብቃት በተግባር ያረጋገጠችበትና በራስ አቅም የመመራት ጉዞዋን ያፋጠነ ትልቅ ምዕራፍ ተደርጎ ይወሰዳል። በዲዛይን፣ በግንባታና በቴክኖሎጂ አጠቃቀም ረገድ ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያውያን መሐንዲሶች እየተመራ ያለው ይህ ፕሮጀክት በአሁኑ ወቅት 87 በመቶ ደርሷል። ለስድስት ወራት የታቀደውና የሦስት ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ይህ ሥራ ከተቀመጠለት የጊዜ ገደብ ቀድሞ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል። በፕሮጀክቱ የተሳተፉ ባለሙያዎች ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በራስ አቅም እየተገነባ በሚገኝ ፕሮጀክት ላይ መሳተፋቸው ትልቅ ዕድል መሆኑን አንስተዋል። የፕሮጀክቱ ማናጀር ንግስት ሀይሉ እንደገለጹት፤ ፕሮጀክቱ በጥሩ ሁኔታ ላይ የሚገኝ ሲሆን በሚቀጥሉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ ተጠናቆ ወደ ሥራ እንደሚገባ ገልጸዋል። ቀደም ሲል የባቡር ግንባታዎች በቱርክና በቻይና ኩባንያዎች ይከናወኑ እንደነበር አንስተው፤ አሁን ግን በራሳችን አቅም መስራት አለብን በሚል ብሄራዊ ቁጭት ወደ ሥራ መገባቱን ተናግረዋል። የፕሮጀክቱ ስኬታማነት ለሀገሪቱ ትልቅ ልምድ ማስገኘቱን ገልጸው፣ የኢትዮጵያን የባቡር ትራንስፖርት ዘርፍ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር የሚያስችል ሙሉ ዝግጁነትን ፈጥሯልም ነው ያሉት። የፕሮጀክቱ የትራክ ወርክ ማናጀር ኦብሳ ጀማል በበኩላቸው፣ ግንባታው ከዲዛይን ጀምሮ እስከ ፍጻሜው ያለ ምንም የውጭ ድጋፍ በሀገር ውስጥ ባለሙያዎች ብቻ መከናወኑ ታላቅ ስኬት መሆኑን ገልጸዋል። ሊያጋጥሙ የሚችሉ ተግዳሮቶችን በስኬት መወጣት መቻላቸው ከፍተኛ በራስ መተማመን እንደፈጠረላቸውም ተናግረዋል። ስራው በሀገር ውስጥ ባለሙያዎች መከናወኑ በተለይም ለውጭ ኮንትራክተሮች ይከፈል የነበረውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ማስቀረቱ ለሀገራችን ጠቃሚ መሆኑን አንስተዋል። የፕሮጀክቱ የመካኒካል ማናጀር ሮባ ጠኖ፣ ኢትዮጵያ በባቡር ቴክኖሎጂ ዘርፍ የነበራትን የውጭ ባለሙያዎች ጥገኝነት በሀገር በቀል እውቀት በመተካት አዲስ የታሪክ ምዕራፍ መክፈቷን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ትልቅ ሀገር በመሆኗ በርካታ የባቡር መሰረተ ልማቶች እንደሚያስፈልጓት የገለጹት ባለሙያው፣ ይህ ፕሮጀክት ለቀጣይ ሥራዎች ትልቅ መሠረት የጣለ መሆኑን ተናግረዋል። ባለሙያዎቹ መንግስት በሀገር ውስጥ አቅም ላይ በመተማመን ይህንን ዕድል በመስጠቱ ምስጋናቸውን አቅርበው፣ በቀጣይም በትልልቅ ፕሮጀክቶች ላይ ውጤታማ ስራ ለመስራት መዘጋጀታቸውን አረጋግጠዋል።
የቡና ጥራትን በማሻሻል በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነትን ለማስጠበቅ እየተሰራ ነው
Mar 5, 2026 90
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦የቡና ጥራትን በማሻሻልና አቅራቢዎች ምርቱን በቀጥታ ወደዓለም ገበያ እንዲያቀርቡ በማስቻል በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነትን ለማስጠበቅ እየተሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) ገለጹ። የቡና አምራቾችና አቅራቢዎች በእጃቸው ያለውን የቡና ምርት በፍጥነት ወደ ገበያ ሊያቀርቡ ይገባል ባለፉት ሁለት ወራት የቡና ዋጋ በዓለም አቀፍ ደረጃ እየቀነሰ በመምጣቱ የቡና አምራቾችና አቅራቢዎች በእጃቸው ያለውን የቡና ምርት በፍጥነት ወደ ገበያ ሊያቀርቡ እንደሚገባም አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን የዓለም አቀፉ የቡና ገበያ ሁኔታ እና የኢትዮጵያ ቡና ወቅታዊ ጉዳዮችን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። በዚህ ወቅት የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ ባለፉት አምስት ዓመታት በመጠንና ጥራት የተሻለ ቡናን ለዓለም ገበያ በማቅረብ የተሻለ ገቢን ማግኘት ተችሏል። የቡና እሴት ሰንሰለትን ማሳጠር፣ የግብይት ስርዓቱን ማስተካከልና ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ መዋቅራዊ ለውጦች መደረጋቸውን ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በዓመት ከ600 ሺህ ሜትሪክ ቶን ያልበለጠ ቡና ሲመረት መቆየቱን አስታውሰው፤ በዘንድሮ በጀት ዓመት 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ሜትሪክ ቶን ቡና መመረቱን ተናግረዋል። በ2017 በጀት ዓመት 470 ሺህ ቶን ቡና ወደ ውጭ በመላክ 2 ነጥብ 6 ቢሊየን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልፀው፣ በዘንድሮ በጀት ዓመትም 600 ሺህ ቶን ቡና በመላክ 3 ቢሊየን ዶላር ገቢ ለማግኘት ታቅዶ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ከ2 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ቡናን ለዓለም አቀፍ ገበያ ማቅረብ እንዲችሉ የላኪ ፍቃድ ማግኘታቸውን ገልፀው፤ 500 ያህሉ ቀጥታ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል። ባለፉት ሁለት ወራት የቡና ዋጋ በዓለም አቀፍ ገበያ እየቀነሰ መምጣቱን አንስተው፤ የጥራት ደረጃን በማሻሻል፣ ስፔሻሊቲ ቡናን በማቅረብና ተወዳዳሪነትን በማሳደግ የታቀደውን ለማሳካት እንደሚሰራ ነው የገለፁት። ቡና በተመረተበት ዓመት መውጣት እንዳለበት በህግ የተቀመጠ ቢሆንም ምርት ዋጋ ይጨምራል በሚል ሃሳብ ይዘው የተቀመጡ በእጃቸው ላይ ያለውን መሸጥ እንዳለባቸው አሳስበዋል። ለአንድ ዓመት ያህል የዓለም አቀፍ የቡና ዋጋ በዚሁ ሊቀጥል እንደሚችል ተገንዝበው በእጃቸው ያለውን ቡና በአፋጣኝ ለገበያ እንዲያቀርቡም አሳስበዋል። ሀገራዊ የኮንትሮባንድ ግብረኃይል መቋቋሙን ጠቁመው፤ በኮንትሮባንድ ለመላክ ጥረት የሚያደርጉ አካላት ላይ ጥብቅ ክትትል እንደሚያደርግም አብራርተዋል።
በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከእጣንና ሙጫ ምርት ሽያጭ ከ280 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለማግኘት ትኩረት ተደርጓል
Mar 5, 2026 67
ገንዳውኃ፤ ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦በምዕራብ ጎንደር ዞን ከእጣንና ሙጫ ምርት ሽያጭ ከ280 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለማግኘት ትኩረት መደረጉን የዞኑ ደን ጥበቃ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በአማራ ክልል ከሚመረቱ ገበያ ተኮር ምርቶች መካከል የተፈጥሮ እጣንና ሙጫ በዋነኝነት የሚጠቀስ ሲሆን ከአንድ የሙጫ ዛፍ በዓመት እስከ 30 ኩንታል የእጣን ምርት ይገኛል። በክልሉ የምርጥ ዘር አቅርቦትን በውስጥ አቅም ለመሸፈን በመቻሉ ለበልግ እርሻ ምቹ ሁኔታን ተፈጥሯል በጽህፈት ቤቱ የአካባቢ የሕግ ተከባሪነትና የማኅበረሰብ ተፅዕኖ ግምገማ ቡድን መሪ አቶ ሀብታሙ አድጎ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በዞኑ የተፈጥሮ እጣንና ሙጫ ደን ለኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማዋል በትኩረት እየተሰራ ነው። በዞኑ በሚገኘው ከ334 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የእጣንና ሙጫ ደን ላይ 41 ማህበራትና ባለሃብቶችን በማሰማራት የማምረት ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በበጀት ዓመቱም ከአምስት ሺህ ኩንታል በላይ የእጣንና ሙጫ ምርት በማምረት ከ280 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለማግኘት በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከሚገኘው ገቢም ከ56 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆነው በሮያሊቲ ገቢ የሚገኝ መሆኑን አመልክተዋል። እስካሁን በተደረገ ጥረትም ከአንድ ሺህ 125 ኩንታል በላይ እጣንና ሙጫ ማምረት መቻሉን ጠቁመው ከዚህም ለመንግስት በሮያሊቲ ክፍያ አምስት ሚሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ ማስገባት መቻሉን አስረድተዋል። በዞኑ መተማ ወረዳ ለምለም ተራራ ቀበሌ በተፈጥሮ ሀብት ህብረት ስራ ማህበር ተደራጅተው እጣንና ሙጫ በማምረት ከተሰማሩ ወጣቶች መካከል ወጣት ኑሬ አዳነ እንዳለው፤ የተፈጥሮ ሀብቱን በመጠበቅ፣ በመንከባከብ ጥቅም ላይ ለማዋል እየሰራ ነው። አስራ አንድ አባላት ያሉት ማህበር በመመስረት ከ100 ኩንታል በላይ የእጣን ምርት አምርተው በመሸጥ ከ8 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ተናግሯል። "የተፈጥሮ ሀብትን በአግባቡ በመጠበቅ ሀብት እያፈራን ነው" ሲል ነው የገለጸው፡። በመተማ ወረዳ የለምለም ተራራ ቀበሌ ነዋሪው ጥላሁን ዋሴ በበኩሉ፤ ባለፈው ዓመት ከመቶ ኩንታል በላይ ምርት ያገኙ መሆኑን አስታውሶ፤ በዚህ ዓመት ከአምናው የተሻለ ምርት ማግኘት እንደሚችሉ አስረድቷል። ባለፈው ዓመት በአካባቢው የተመረተውን የእጣንና ሙጫ ምርት በመሸጥ ከ108 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱንም የጽህፈት ቤቱ መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ ከተሞች ትብብር መድረክ ለከተሜነት መስፋፋት በትኩረት እየሰራ ነው
Mar 5, 2026 153
አዳማ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከተሞች ትብብር መድረክ ለከተሜነት መስፋፋት፣ ለተሻለ እና ምቹ ኑሮ እውን መሆን በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገለጸ። ፍትሃዊ የመሰረተ-ልማት ስርጭትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ስኬታማ ተግባራት ተከናውነዋል መድረኩ ከስድስት ክልሎችና ከሁለት ከተማ አስተዳደሮች ለተውጣጡ ከንቲባዎችና የዘርፉ አመራሮች ያዘጋጀው የ"ስማርት ሲቲ" ትግበራ እና የ"ፕሌስ ሜኪንግ" (ሁሉን አቀፍ የህዝብ ቦታዎች ልማት) ስልጠናዊ አውደ ጥናት በአዳማ ከተማ እያካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ከተሞች ትብብር መድረክ ዋና ዳይሬክተር አቶ አንዷለም ጤናው እንደገለጹት፤ መድረኩ በአሁኑ ወቅት ከ150 በላይ ከተሞችን በአባልነት በመያዝ፣ ለከተሜነት መስፋፋት፣ ለተሻለና ምቹ ኑሮ እውን መሆን በትኩረት እየሰራ ነው። እንደ ዋና ዳይሬክተሩ ገለጻ፣ መድረኩ ከተሞች ጽዱ፣ ውብና ለነዋሪዎቻቸው ምቹ እንዲሆኑ ከማስቻል ባለፈ ከተሞች ያላቸውን ሀብት በአግባቡ አውቀው የማዘጋጃ ቤታዊ ገቢ አሰባሰባቸውን እንዲያሳድጉ አጋዥ እየሆነ ነው። ከተሞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ የ"ስማርት ሲቲ" አሰራርን በመዘርጋት የአገልግሎት ጥራትና የዜጎችን ደህንነት እንዲያረጋግጡ እንዲሁም የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር ከተሞችን መልካም ተሞክሮ በመቀመር የአቅም ግንባታ ስራዎችን እንዲያከናውኑ ድጋፍ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። በተለይም "ፕሌስ ሜኪንግ" የተሰኘው ስልጠና ዘላቂና ሁሉን አቀፍ የህዝብ መዝናኛና መናፈሻ ቦታዎችን ለማልማት የሚረዳ ሲሆን፤ ይህም ባለፉት አራት ዓመታት በከተሞች ልማት የታየውን ተጨባጭ ለውጥ ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ገልጸዋል። ከስልጠናው ተሳታፊዎች መካከል የጨለለቅቱ ከተማ ከንቲባ አቶ ተስፋነህ ታደለ ፤ አስተዳደሩ ጨለለቅቱ ከተማን ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሰፊ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ይህ ስልጠና እንቅስቃሴያችንን በቴክኖሎጂ ለማሳለጥ ተጨማሪ አቅም ይሆነናል ሲሉም ተናግረዋል። የቦዲቲ ከተማ ከንቲባ አቶ ዘካርያስ ጃታ በበኩላቸው፤ መድረኩ እንደ ሀገር የተጀመሩ የከተማ ኮሪደር ልማት ኢንሼቲቮችን ለመደገፍና ከተሞችን በዲጂታላይዜሽን መርህ ወደ ስማርት ሲቲ ለመቀየር የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል። ተሳታፊ ከንቲባዎች ከስልጠናው የሚያገኙትን እውቀትና ልምድ በመጠቀም፣ በከተሞቻቸው የሚታየውን የገቢ አሰባሰብና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግሮችን ለመቅረፍ ጥረት እንደሚያደርጉም አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ተገቢና ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ወሳኝ ነው
Mar 5, 2026 106
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ተገቢና ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን በኢትዮጵያ የኖርዌይ እና የባንግላዲሽ አምባሳደሮች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በቅርቡ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማብራሪያ በሰጡበት ወቅት ኢትዮጵያና ቀይ ባሕር በሕግ፣ በመልክዓምድር፣ በታሪክና ሌሎች መለኪያዎች ሊነጣጠሉ እንደማይችሉ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የኖርዌይ አምባሳደር ስቲያን ክሪስቴንሰን እና በኢትዮጵያ የባንግላዲሽ አምባሳደር ኤር ቫይስ ማርሻል ሲትዋት ናይም ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የጋራ ዕድገትን ለማረጋገጥ አስተማማኝ የባሕር በር ወሳኝ ነው። የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄዋን ምላሽ ለማስገኘት የምትከተለው ሕጋዊ፣ ሰላማዊና የጋራ ተጠቃሚነት መርህን ሀገሮቻቸው እንደሚገነዘቡም አምባሳደሮቹ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄና የባሕር በርና የአማራጭ ወደብ አገልግሎት ለጋራ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትና ቀጣናዊ ሰላምና ደኅንነት ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የኖርዌይ አምባሳደር ስቲያን ክሪስቴንሰን፤ ኢትዮጵያ በአስደናቂ ኢኮኖሚ ዕድገት ላይ የምትገኝ ከፍተኛ የመልማት አቅም ያላት ሰፊ ሀገር ናት ብለዋል። ይህንን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴ የሚመጥን አስተማማኝ የባሕር በር የማግኘት ጥያቄ ጉልህ ፋይዳ ያለው ሀገራዊ ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያን አስተማማኝ የባሕር በር የማግኘት ጥያቄ አስፈላጊነት በቅጡ እንረዳለን ያሉት አምባሳደሩ፤ ኢትዮጵያም በቀጣናው ሀገራት የባሕር በር ማግኘት የምትችልበት ሰፊ ዕድል መኖሩን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የባንግላዲሽ አምባሳደር ኤር ቫይስ ማርሻል ሲትዋት ናይም፤ ለአንድ ሀገር ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ የንግድና ኢንቨስትመንት፣ ሰላምና ደኅንነት አስተማማኝ የባሕር በር አስፈላጊ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄም እያደገ ከሚገኘው የንግድና ኢንቨስትመንት የኢኮኖሚ ዕድገቷ አንጻር ሕጋዊነቱን እንደሚያጎላው አንስተዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያ የባሕር በር የማግኘት ጥያቄ ምላሽ ለማስገኘት ከቀጣናው ሀገራት ጋር በሰጥቶ መቀበልና በጋራ ተጠቃሚነት መርህ በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።
በክልሉ የህዝብን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር)
Mar 5, 2026 65
ሀደሮ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ የሚተገበሩ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) ገለፁ፡፡ በክልሉ መንግሥት በጀት በከምባታ ዞን በተለያዩ መዋቅሮች ተገንብተው የተጠናቀቁ የመንገድ፣ የንፁህ መጠጥ ውሃና የመስኖ ፕሮጀክቶች በክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ የህዝብ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶችን እውን ለማድረግ የተጀመሩ ተግባራት በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ። የክልሉ መንግስት ለማህበረሰቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ምላሽ ለመስጠት ከምንጊዜውም በላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡ ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት የተደረጉት የንፁህ መጠጥ ውሃ፣ የመስኖ እና የመንገድ ፕሮጀክቶች የዚሁ አካል መሆናቸውንም ጠቁመዋል፡፡ በክልሉ የትምህርት ቤት፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትና የኤሌክትሪክ ሀይል ተደራሽነትን ለማስፋት በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ነው የገለጹት። የክልሉ መንግስት በዞኑ ሀደሮ ጡንጦ ዙሪያ ወረዳ አንድ የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በአጭር ጊዜ ውስጥ ገንብቶ እንደሚያስረክብም አረጋግጠዋል፡፡ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ መሀመድ ኑርዬ(ዶ/ር) እንዳሉት፣ በክልሉ ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ጀምሮ የማጠናቀቅ ልምድ እየዳበረ መጥቷል ብለዋል፡፡ ማህበረሰቡ ዛሬ የተመረቁ ፕሮጀክቶችን በአግባቡ በመጠበቅ ለታለመላቸው ጥቅም እንዲውሉ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እንዲወጣም አስገንዝበዋል፡፡
በክልሉ የምርጥ ዘር አቅርቦትን በውስጥ አቅም ለመሸፈን በመቻሉ ለበልግ እርሻ ምቹ ሁኔታን ተፈጥሯል
Mar 5, 2026 76
ዲላ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የምርጥ ዘር አቅርቦትን በውስጥ አቅም ለመሸፈን በመቻሉ በበልግ እርሻ የግብዓት ስርጭትን ውጤታማ ማድረጉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በክልሉ የብድር አቅርቦትን ጨምሮ ትራክተርና ሌሎች የግብርና ግብዓቶችን ለአርሶ አደሩ በማቅረብ የሚታረስ መሬትን ለማስፋትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑም ተመላክቷል። የቢሮው ምክትልና የግብርና ግብዓት ገጠር ፋይናንስ አቅርቦት ዘርፍ ኃላፊ ግዳልቅ አልቅሚ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በክልሉ የበልግ ዝናብ ፈጥኖ መጀመሩን ተከትሎ የግብዓትና ቴክኖሎጂ ስርጭት ስራ ተጀምሯል። በዚሁ ወቅት ከ287 ሺህ ኩንታል በላይ ዳፕና ዩሪያ ለማቅረብ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑንና ከዚህ ውስጥ 160 ሺህ 64 ኩንታል ማዳበሪያ ስርጭት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ለበልግ እርሻ ከሚያስፈልገው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ 56 በመቶውን የሚሸፍን ሲሆን ቀሪ ስርጭትም በቀጣይ ሳምንት እንደሚከናወን ገልጸዋል። በተለይ ለበቆሎ፣ ለማሽላ፣ ለማሾ፣ ለቦሎቄ፣ ጤፍን ጨምሮ ለዋና ዋና ሰብሎች ከሚያስፈልገው 65 ሺህ ኩንታል ምርጥ ዘር ውስጥ 63 ሺህ 560 ኩንታል ምርት በማምረት በየማዕከላቱ ቀድሞ ማከማቸት መቻሉን አስረድተዋል። በዘንድሮው ዓመትም የ37 ትራክተሮች ግዢ መፈፀሙን የተናገሩት ኃላፊው በአጠቃላይ ለበልግ እርሻ 415 ትራክተሮች ወደ ስራ መሰማራታቸውን አስረድተዋል። በበልግ እርሻ በአዝርዕት፣ በአትክልትና ስራስር ሰብሎች ከሚለማው 987 ሺህ 314 ሄክታር መሬት ውስጥ 209 ሺህ 366 ሄክታሩ በትራክተር እየታረሰ መሆኑንም ነው ያነሱት። ይህም በክልሉ ሜካናይዘሽንን በማስፋት የአርሶ አደሩን ጊዜና ጉልበት በመቆጠብ ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል። የበልግ ወቅት የክልሉ ዋና የእርሻ ጊዜ በመሆኑ አርሶ አደሩ ያገኘውን ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በአግባቡ ስራ ላይ በማዋል ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግ መስራት አንደሚጠበቅበትም አስገንዝበዋል።
በጂንካ ከተማ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የተሰማሩ ዜጎች ውጤታማ እየሆኑ ነው
Mar 5, 2026 70
ጂንካ፤ የካቲት 26/2018 (ኢዜአ):-በጂንካ ከተማ አስተዳደር በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በወተት ልማትና በዶሮ እርባታ ሥራ የተሰማሩ ነዋሪዎች ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናገሩ። በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና ስርዓተ ምግብን ለማሻሻል ወሳኝ ሚና ያለው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በየአካባቢው ዜጎችን ተጠቃሚ እያደረገ ነው። በጂንካ ከተማ በመርሀግብሩ እየተሳተፉ ያሉ ነዋሪዎችም ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ለኢዜአ ተናግረዋል። ከተጠቃሚዎቹ መካከል አቶ ገዛህኝ አዲሱ እንዳሉት በሁለት የወተት ላሞች በመኖሪያ ግቢያቸው የጀመሩት የእርባታ ሥራ ዛሬ ላይ እየተስፋፋ መምጣቱን ተናግረዋል። በተለይም በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለዘርፉ ትኩረት መሰጠቱ ለውጤታቸው አስተዋጾ ማድረጉን ገልጸው፣ የወተት ምርታቸውን ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ በየቀኑ ከ40 ሊትር በላይ ወተት ለማህበረሰቡ በማቅረብ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል። በሥጋ ዶሮ እርባታ ሥራ ላይ የተሰማሩት አቶ ኡመር ጀማልም በግብርና ባለሙያዎች ታግዘው ምጥን መኖ በማዘጋጀት የሥጋ ዶሮዎችን እያረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የዶሮ እርባታ አዋጭ ሥራ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ኡመር፣ የ45 ቀን ጫጩቶችን ተረክበው በማሳደግና በስድስት ወራት ውስጥ ለሽያጭ በማቅረብ ትርፋማ እየሆኑ መምጣታቸውን ገልጸዋል። ወይዘሮ ሩሃማ እንግዳ በበኩላቸው ከሌሎች አካባቢዎች ባገኙት ተሞክሮ በመኖሪያ ግቢያቸው በዘመናዊ መልክ የአሣ ጫጩቶችን እያረቡ ይገኛሉ። በአካባቢው የአሣ እርባታ ሥራ ባለመለመዱና አቅርቦቱም በቂ ባለመሆኑ ለስራው እንዳነሳሳቸው ገልጸው ባላቸው አነስተኛ ግቢ በ50 የአሣ ጫጩቶች ሥራውን መጀመራቸውን ተናግረዋል። "በሙከራ ደረጃ የጀመርኩት የአሣ እርባታ ሥራ አሁን ላይ ውጤታማ እየሆነ በመምጣቱ ዓሣን በስፋት በማምረት ለገበያ ለማቅረብ አቅጂያለሁ" ብለዋል። በጂንካ ከተማ አስተዳደር የግብርና ዩኒት አስተባባሪ አቶ አይናለም ጨነቀ እንዳሉት በከተማው የዶሮ፣ የሥጋ፣ የወተት፣ የማርና የዓሣ መንደር በመመስረት ከ8ሺህ 700 በላይ ተጠቃሚዎች በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር እንዲሳተፉ ተደርጓል። የሌማት ትሩፋት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ በከተማው በወተት፣ በዕንቁላል፣ በዶሮና በማር አቅርቦት መሻሻል እንዲመጣ አድርጓል ብለዋል። ለነዋሪዎቹ የተሻሻሉ ዶሮዎች፣ የወተት ላሞችና የአሣ ዝርያዎችን በማቅረብ ተጠቃሚ የማድረግ ሥራ እየተሰራ መሆኑንም ነው የተናገሩት። ነዋሪዎቹ በተጨማሪም አትክልትና ፍራፍሬዎችን በዘመናዊ መልክ በማልማትና በመጠቀም የአመጋገብ ስርአታቸውን እንዲያሻሽሉ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። ከግለሰቦች በተጨማሪ የተለያዩ ተቋማት በሌማት ትሩፋት መርሀግብር በመሳተፍ የውስጥ ገቢያቸውን ከማሳደግ ባለፈ ለአካባቢው ማህበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ ምርት በማቅረብ እያገዙ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
የቡና አምራቾችና አቅራቢዎች በእጃቸው ያለውን የቡና ምርት በፍጥነት ወደ ገበያ ሊያቀርቡ ይገባል
Mar 5, 2026 103
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ የቡና አምራቾችና አቅራቢዎች በእጃቸው ያለውን የቡና ምርት በፍጥነት ወደ ገበያ ሊያቀርቡ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን አሳሰበ። ባለፉት ሁለት ወራት የቡና ዋጋ በዓለም አቀፍ ደረጃ እየቀነሰ መምጣቱንም ዋና ዳይሬክተሩ አዱኛ ደበላ(ዶ/ር) ገልፀዋል። የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ(ዶ/ር) የዓለም አቀፉ የቡና ገበያ ሁኔታ እና የኢትዮጵያ ቡና ወቅታዊ ጉዳዮችን አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል። በዚህ ወቅት የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ(ዶ/ር) እንዳሉት፣ ባለፉት አምስት ዓመታት በመጠንና በጥራት የተሻለ ቡና ለዓለም ገበያ በማቅረብ የተሻለ ገቢ ማግኘት ተችሏል። የቡና እሴት ሰንሰለትን ማሳጠርና ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቁመው፤ በዘንድሮ በጀት ዓመት 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ሜትሪክ ቶን ቡና መመረቱን ተናግረዋል። በ2017 በጀት ዓመት 2 ነጥብ 6 ቢሊየን ዶላር በላይ ከቡና ወጪ ንግድ ገቢ መገኘቱን ገልፀው፣ በዘንድሮ በጀት ዓመትም 3 ቢሊየን ዶላር ገቢ ለማግኘት ታቅዶ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ባለፉት ሁለት ወራት የቡና ዋጋ በዓለም አቀፍ ገበያ እየቀነሰ መምጣቱን አንስተው፤ የጥራት ደረጃን በማሻሻል፣ ስፔሻሊቲ ቡናን በማቅረብና ተወዳዳሪነትን በማሳደግ የታቀደውን ለማሳካት እንደሚሰራም አስታውቀዋል። ከ2ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ቡናን ለዓለም አቀፍ ገበያ ማቅረብ እንዲችሉ የላኪነት ፈቃድ ማግኘታቸውን ጠቁመው፤ 500 ያህሉ ቀጥታ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል። ቡና በተመረተበት ዓመት መውጣት እንዳለበት በህግ የተቀመጠ ቢሆንም ዋጋ ይጨምራል በሚል ምርት ይዘው የተቀመጡ አካላት ለአንድ ዓመት ያህል የዓለም አቀፍ የቡና ዋጋ በዚሁ ሊቀጥል እንደሚችል ተገንዝበው በእጃቸው ያለውን ለገበያ ማቅረብ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ሀገራዊ የኮንትሮባንድ ንግድን የሚከላከል ግብረ ኃይል መቋቋሙን ጠቁመው፤ በኮንትሮባንድ ለመላክ ጥረት የሚያደርጉ አካላት ላይ ክትትል እንደሚያደርግም አብራርተዋል።
ኢትዮጵያን ያለ ባህር በር ዘግቶ መኖር የማይቻልና መቀጠል የሌለበት የህልውና ጉዳይ ነው
Mar 5, 2026 140
ሐረር፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያን ያለ ባህር በር ዘግቶ መኖር የማይቻልና መቀጠል የሌለበት የህልውና ጉዳይ መሆኑን የቀድሞ የጦር አባላት ተናገሩ። የባህር በር ከንግድና የምጣኔ ሃብት ፋይዳ ባሻገር ዓለም አቀፋዊ ትስስር፤ የጋራ ተጠቃሚነት፣ የሰላምና ጸጥታ ጉዳዮችና ሌሎች ጥቅሞችን ማረጋገጥ የሚቻልበት ወሳኝ መሰረተ ልማት መሆኑ ይታወቃል። በዚሁ መሰረት ኢትዮጵያ ለዘመናት ይዞታዋ በነበረው የባህር በር ጥቅሟንና ክብሯን አስጠብቃ የኖረች ቢሆንም የዛሬ 30 ዓመት በውል ባልታወቀ ምክንያት ከባህር እንድትርቅ ተደርጓል። የምጣኔ ሃብቷ በእድገትና ማንሰራራት ላይ የሚገኘውና በአፍሪካ ሁለተኛውን የህዝብ ቁጥር የያዘችው ኢትዮጵያን ከባህር የቅርብ እሩቅ አድርጎ መዝለቅ የማይቻልና የህልውና ጉዳይ ሆኗል። በመሆኑም የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጉዳይ የትውልድ ጥያቄ ሆኖ ለተግባራዊነቱ ጥረቱ ተጠናክሮ የቀጠለ መሆኑ ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በቅርቡ በመከላከያ ሰራዊት የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ 65ኛ ዓመት አከባበር ላይ ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያ ባህርን ለብሄራዊ ጥቅሟና ለቀጣናዊ ሰላምና ደህንነት ጭምር የመጠቀም ዓላማ ሰንቃ እየሰራች መሆኑን መግለጻቸው ይታወሳል። ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተገናኘ ኢዜአ ያነጋገራቸው በሐረር ከተማ የሚገኙ የቀድሞ ጦር አባላት፤ የኢትዮጵያ እና የባህር በር ተነጣጥሎ መኖር የሁላችንም ጥያቄና ቁጭት ሆኖ የቆየ ነው ብለዋል። በመሆኑም አሁን ላይ የሀገር ህልውና እና የትውልድ ጥያቄ ሆኖ መምጣቱ ተገቢ መሆኑን አንስተው ለምላሹ የሁላችንም ጥረት ያስፈልጋል ነው ያሉት። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል መቶ አለቃ ውቤ ታሪኩ፤ ኢትዮጵያ ምክንያቱ በውል ባልታወቀ ሁኔታ ከባህር እንድትርቅ መደረጉ ትልቅ የታሪክ ስብራት መሆኑን አንስተው ወደ ባህር የምትመለስበት ጊዜ እሩቅ እንደማይሆንም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤት መሆን ከራሷ ብሄራዊ ጥቅም ባለፈ ለቀጣናዊ ትስስር፣ ሰላምና ደህንነት መረጋገጥ የላቀ ፋይዳ ያለው መሆኑን አንስተዋል። ኢትዮጵያ በልማት እየበለጸገችና ኢኮኖሚዋን የሚያሳልጥ የገቢና ወጪ ንግድ ስራዎች እያደገ እንደሚገኝ ጠቁመው ይህን ኢኮኖሚ መሸከም የሚችል የባህር በር ይገባናልና ማስመለስ አለብን ነው ያሉት። ኢትዮጵያን የባህር በር ባለቤት ለማድረግ ትውልዱ የጀመረውን ጥረት አድንቀው የተጀመረው ጥረት ከግብ እንዲደርስ የሁላችንም አደራ ሆኖ ይቀጥላል ብለዋል። ሌላኛው የቀድሞ የጦር አባል ሃምሳ አለቃ በፍቃዱ ፈይሳ፤ ጀግኖች ኢትዮጵያውያን ደማቸውን የገበሩበት የባህር በር በሴራ ፖለቲካ እንድታጣ የተደረገበት መንገድ የዘመናት ቁጭት መሆኑን ገልጸዋል። መንግስት የሀገሪቱን ልማትና ሰላም እያጎለበተና የህዝቡን ተጠቃሚነት እያሳደገ ይገኛል ለዚህም ታላላቅ የሀገራት መሪዎች ምስክርነታቸውን እየሰጡ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም በታሪክ፣ በመልክአ ምድርና በህግ አግባብ የኢትዮጵያ አካል የነበረው የባህር በር የሚመለስበት ጊዜ እሩቅ መሆን የለበትም ብለዋል።
በጉጂ ዞን የቡና ልማትን ለማስፋፋት ከ70 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል
Mar 5, 2026 114
ነገሌ ቦረና፤ የካቲት 26/2018 (ኢዜአ)፡- በጉጂ ዞን የቡና ልማትን ለማሻሻልና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ከ70 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኞች መዘጋጀታቸውን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የቡናና ሻይ ልማት ባለሙያ አቶ ብርሀኑ ፈይሳ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በዘንድሮው ዓመት የዞኑን የቡና ልማት ለማስፋፋት የሚያስችሉ ከ61 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል። ባለፉት ሰባት ወራትም ከ70 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን በማዘጋጀት ከእቅድ በላይ መፈፀም መቻሉን አብራርተዋል። የተዘጋጁት ችግኞች በመጪው የክረምት ወቅት የሚተከሉ ሲሆን የተሻሻሉና የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ መሆናቸውንም አመልክተዋል። የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎቹ በአብዛኛው ከጅማ ግብርና ምርምር እና ከይርጋለም አወዳ የምርምር ጣቢያ የተለቀቁ ሲሆን በሄክታር ከ12 እስከ 15 ኩንታል ምርት ለመስጠት የሚያስችሉ መሆናቸውን አንስተዋል።፡ ዝርያው ብርድና በሽታን በመቋቋም በቅርብ ዓመታት ምርት ለመስጠት የሚያስችል እንደሆነም በምርምር ማዕከላቱ መረጋገጡን ነው የገለጹት፡፡ የቡና ልማቱን በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች ለማስፋፋት 10 ሺህ 500 ሄክታር አጠቃላይ መሬት መዘጋጀቱን አመልክተው የተሻሻለውን የቡና ዝርያ ለ61 ሺህ አምራች አርሶ አደሮች ተደራሽ ለማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅትም በዞኑ በ12 ወረዳዎችና በ157 ቀበሌዎች ከ177 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቡና ልማት መሸፈኑንም ገልጸዋል። በዞኑ ከሰብል ልማት እና ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን ከ108 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በቡና ልማት ስራ ላይ እየተሳተፉ እንደሚገኙም ባለሙያው ጠቁመዋል፡፡
በወለጋ ዞኖች የተጀመሩ የልማት ስራዎች የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ እና የአካባቢውን እምቅ አቅም ለመጠቀም የሚያስችሉ ናቸው
Mar 5, 2026 79
ነቀምቴ፣ የካቲት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በወለጋ ዞኖች የተጀመሩ የልማት ስራዎች የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ እና የአካባቢውን እምቅ አቅም ለመጠቀም የሚያስችሉ ናቸው ሲሉ በወለጋ ዩኒቨርሲቲ የሚሰሩ መምህራን ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ በኦሮሚያ ክልል በቄለም ወለጋ፣ በምስራቅ ወለጋ እና ምዕራብ ወለጋ ዞኖች እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን መጎብኘታቸው ይታወሳል። በወቅቱም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአካባቢው አመርቂ እድገት እና ለውጥን የሚያሳዩ ዐበይት የልማት ሥራዎችን መመልከት መቻላቸውን ገልጸው በተለይም የግብርና፣ የማዕድን እና የኮሪደር ልማት ስራዎች ተስፋ ሰጪ መሆናቸውን አንስተዋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ከወለጋ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል መምህራን ጋር ቆይታ ያደረገ ሲሆን መምህራኑም በዞኖቹ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ለሁለንተናዊ እድገት መሰረትን የሚጥሉ ናቸው ብለዋል። በዩኒቨርሲቲው የኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል መምህርና ተባባሪ ፕሮፌሰር ገመቹ ሙላቱ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ በአካባቢው ባለፉት ዓመታት አጋጥሞ የነበረው የጸጥታ ችግር መቀረፉ ለልማት ስራዎች ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል። በአካባቢው የተገኘው ሰላም የመንገድ፣ የትምህርት፣ የጤና፣ የኃይል፣ የንጹህ ውሃና የቴሌኮም መሠረተ ልማት እንዲስፋፉ አድርጓል ብለዋል። ይህም የአካባቢውን እምቅ የልማት አቅም ጥቅም ላይ እንዲውል ከማስቻሉም በላይ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ህዝቡን ተጠቃሚ ለማድረግ መሰረት ይጥላል ነው ያሉት። እነዚህ ስራዎች የገበያ ትስስርን ከማጠናከር ባለፈ ለቀጣዩ ትውልድ ተስፋ ሰጪ መሆናቸውን ጠቅሰው ለፕሮጀክቶቹ ውጤታማነት በጋራ መቆም እንደሚገባ አስረድተዋል። ዩኒቨርሲቲውም በምርምርና በቴክኖሎጂ ሽግግር ረገድ የአካባቢውን ልማት የሚያፋጥኑ ስራዎች ላይ አተኩሮ በመስራት ድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል። ሌላኛው በዩኒቨርሲቲው የኢኮኖሚክስ መምህር እሱባለው ዳባ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ መንግስት ህብረተሰቡን በማስተባበር እያከናወነ የሚገኘው ስራ የሚበረታታ ነው ብለዋል። በወለጋ ዞኖች የተገኘውን ሰላም በመጠቀም ሀብትን ወደ ልማት በመቀየር ረገድ የተጀመረው ስራ ከአካባቢው አልፎ ለአገርም ተስፋ መሆኑን አብራርተዋል። በተለይም በከተሞች እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ስራ የከተሞችን ገጽታ በመቀየር ለኢንቨስትመንት ሳቢ ማድረጉን ጠቅሰው የህዝቡን ጤና ለመጠበቅ የሚያግዝ ነው ብለዋል። በተጨማሪም አምራች አርሶ አደሮች ምርታቸውን በቀጥታ ለማዕከላዊ ገበያ እንዲያቀርቡና ተገቢውን ዋጋ እንዲያገኙ በር መክፈቱን ገልጸዋል። በቀጣይም ዩኒቨርሲቲው የታዩ ጠንካራ ጎኖችን በማስቀጠልና ጉድለቶችን በህዝብ ተሳትፎ በመሙላት፣ የልማት ስራዎቹን ይበልጥ ውጤታማ የማድረግ ሚናውን ያጠናክራል ብለዋል።
በከምባታ ዞን የተገነባው ንፁህ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ
Mar 5, 2026 62
ወንጀላ፤ የካቲት 26/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከምባታ ዞን ከ27 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተገነባው የወንጀላ ንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ። በዞኑ ዶዮገና ወረዳ የተገነባውን የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ያደረጉት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) ናቸው። የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቱ በክልሉ ውሃ፣ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ ከ27 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተገነባ ሲሆን ከ7 ሺህ በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ተመላክቷል። የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቱ 1ሺህ ኪዩቢክ ሜትር ውሃ የሚይዝ ጋን እንደተገነባለትም በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ ተገልጿል። ርዕሰ መስተዳድሩ ከመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቱ በተጨማሪ በዞኑ በተለያዩ አካባቢዎች በክልሉ መንግሥት የተገነቡ የመስኖ፣ የመንገድና የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ያደርጋሉ ተብሎም ይጠበቃል፡፡ በልማት ፕሮጀክቱ የምረቃ መርሐ ግብሩ የክልሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋጤ ስርሞሎ እና ሌሎች የክልል ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በባሌ ሮቤ የተጀመረው የፓስፖርት አገልግሎት የተገልጋዮችን እንግልትና ወጪ መቀነስ አስችሏል
Mar 5, 2026 248
ሮቤ፣ የካቲት 26/2018 (ኢዜአ)፦ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት በባሌ ሮቤ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ከፍቶ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ይደርስባቸው የነበረውን እንግልትና ወጪ ማስቀረቱን ተገልጋዮች ገለጹ። የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ተደራሽነትን ለማስፋፋት ባከናወናቸው የሪፎርም ሥራዎች፣ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተጨማሪ ቅርንጫፎችን መክፈቱ ይታወሳል። በቅርቡ በባሌ ሮቤ የተከፈተው ቅርንጫፍም የዚሁ ጥረት አካል ሲሆን ኢዜአ ያነጋገራቸው ተገልጋዮች እንደገለጹት፤ ተቋሙ አገልግሎቱን ወደ አቅራቢያቸው ማምጣቱና አሰራሩን ማዘመኑ ቀደም ሲል የነበረውን አድካሚ ሂደት አስቀርቷል። የአጋርፋ ወረዳ ነዋሪዋ ሰሚራ አብዱሪ "ቀደም ሲል የፓስፖርት አገልግሎት ለማግኘት ወደ አዳማ፣ ሐዋሳና አዲስ አበባ በመጓዝ ቀናትን የሚወስድ ምልልስ ማድረግ ይጠበቅብን ነበር'' ብለዋል። አሁን ግን በኦንላይን የጀመሩትን ሂደት በቀጠሯቸው መሰረት ፓስፖርት ለመረከብ መምጣታቸውን ገልጸዋል። የሮቤ ከተማ ነዋሪዋ ሰአዳ ሁሴን ፓስፖርት ለማውጣትና ለማደስ ወደ ሌላ ሩቅ አካባቢ መሄድ ግዴታ በመሆኑ ተገልጋዩ ከፍተኛ ምሬት ውስጥ እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን አገልግሎቱ በአቅራቢያቸው መጀመሩ ትልቅ እፎይታ መሆኑን ተናግረዋል። የሮቤ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ ጀማል አባገሮ በበኩላቸው፣ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት በከተማዋ ቅርንጫፍ መክፈቱ ህዝቡ ሲያነሳው የቆየውን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ የመለሰ መሆኑን ጠቅሰዋል። ለሥራው ስኬታማነት አስፈላጊውን ትብብር እንደሚያደርጉም አረጋግጠዋል። የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት በባሌ ሮቤ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ አዲስአለም ንጉሴ እንደገለጹት፤ ቅርንጫፉ የሮቤና የባሌ ዞን ነዋሪዎችን በቅርበት ለማገልገል ያስችላል። አክለውም ተገልጋዮች በኦንላይን መረጃቸውን አጠናቅቀው በተሰጣቸው ቀጠሮ ብቻ ወደ ቅርንጫፉ በመምጣት አገልግሎት ማግኘት እንደሚችሉ ገልጸዋል። የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ባከናወናቸው የሪፎርም ሥራዎች፣ ዘመናዊና ቀልጣፋ አሰራርን እየገነባ መሆኑን ተቋሙ በተለያዩ ጊዜያት መግለጹ ይታወሳል።