ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በአዲስ አበባ እና ድሬዳዋ ከተሞች የኮሪደር ልማትና ሌሎች ፕሮጀክቶች ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥረዋል
Jun 23, 2026 11
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ እና ድሬዳዋ ከተሞች የኮሪደር ልማትና ሌሎች ፕሮጀክቶች ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የሥራ እድል መፍጠራቸውን የሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊዎች ገለጹ፡፡ በአዲስ አበባ ተጀምሮ የከተማ ገጽታን በመቀየርና የነዋሪዎችን ህይወት በማዘመን ረገድ አንጸባራቂ ውጤት የተመዘገበበት የኮሪደር ልማት አሁን ላይ ወደ ክልል ከተሞች ተስፋፍቶ ቀጥሏል፡፡ በአዲስ አበባ እንደታየው ሁሉ በክልል ከተሞች የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገዶች፣ የብስክሌት መስመሮች፣ የንግድና የሕዝብ መዝናኛ ሥፍራዎች ደረጃቸውን ጠብቀው ተገንብተዋል፡፡ ይህም ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድልን የፈጠረው የልማት ሥራ የከተሞችን ውበት እና ለኑሮ ያላቸውን ምቾት በእጅጉ እየጨመረው ይገኛል።   የአዲስ አበባ እና የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች የሥራና ክህሎት ቢሮ የሥራ ኃላፊዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተሞች የተከናወኑ እና በመከናወን ላይ ያሉ ሁለንተናዊ የልማት ሥራዎች ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለወጣቱ ሰፊና ዘላቂ የሥራ እድል መፍጠር ችለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥራ እና ክህሎት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አስፋው ለገሰ፤ ኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሜጋ ፕሮጀክቶች በርካታ ዜጎችን በሥራ ዕድልና በንግድ ሥራ ተጠቃሚ ማድረጋቸውን አንስተዋል።   በከተማዋ በተከናወኑ የወንዝ ዳርቻ ልማት፣ የፓርኮች ግንባታ እና የቤት ልማት ፕሮጀክቶች ከፍተኛ ቁጥር ላላቸው ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቁመዋል፡፡ ቢሮው በ2018 በጀት ዓመት እስካሁን ድረስ ከ365 ሺህ በላይ ዜጎች በተለያዩ መስኮች ወደ ሥራ መሰማራታቸውን ተናግረዋል፡፡ በከተማዋ ኢንዱስትሪ፣ ኮንስትራክሽን፣ የከተማ ግብርና፣ አገልግሎት በስፋት የሥራ ዕድል የተፈጠረባቸው የሥራ መስኮች መሆናቸውን አመላክተዋል፡፡   የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ሮቤል ጌታቸው በበኩላቸው፣ ከተማ አስተዳደሩ በበጀት ዓመቱ እስካሁን ለ19 ሺህ 642 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ጠቅሰዋል፡፡   ለዚህም በከተማዋ የተከናወኑ እና በመከናወን ላይ ያሉ ሁለንተናዊ የልማት ሥራዎች ጉልህ ድርሻ ማበርከታቸውን ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያን የፍየልና በግ የእንስሳት ሃብቶች ምርታማነት የማሳደግ የዝርያ ማሻሻል ሥራ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው
Jun 22, 2026 730
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ):- የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የፍየልና በግ የእንስሳት ሃብት ዝርያን የሚያሻሽሉ ሙያተኞችን ለማፍራት በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቋል። በዚህም ኢንስቲትዩቱ ከሰኔ 08 እስከ 15 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ በሰው ሰራሽ ማዳቀል የፍየልና በግ የእንስሳት ሃብት ዝርያን ለማሻሻል ለሙያተኞች የሰጠውን ስልጠና በማጠናቀቅ ሰልጣኞችን አስመርቋል። የግብርና ሚንስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ፤ ኢትዮጵያ ከፍተኛ የእንስሳት ሃብት ያላት ሀገር ናት ብለዋል። የኢትዮጵያን የፍየልና በግ የእንስሳት ሃብት ምርታማነትን ለማሻሻልም የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችንና የአሰራር ሥርዓቶችን በመቅረፅ እየተሰራባቸው መሆኑን ገልጸዋል። የፍየልና በግ የእንስሳት ሃብት ምርታማነትን ለማሻሻል እየተሰራበት የሚገኘው የሰው ሰራሽ ማዳቀል ሥነ-ዘዴ ተጨባጭ ውጤት እየተገኘ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩትም የሰው ሰራሽ ማዳቀል ሙያተኞችን በብዛትና በጥራት ለማፍራት መሰረት መጣሉን አንስተዋል። በኢንስቲትዩቱ ትምህርትና ስልጠና የተሰጣቸው ሙያተኞችም የእንስሳት ሃብት ምርታማነትን በማሻሻል ህዝባቸውን ማገዝ እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አስራት ጤራ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የመደመር መንግሥት የገጠር ሽግግርን ለማሳለጥ ለእንስሳት ሃብት ምርታማነት ትኩረት እንደሚሰጥ ገልጸዋል። በዚህም የመንግሥትን መርህ ታሳቢ በማድረግ በሰው ሰራሽ የማዳቀል ሥነ-ዘዴ የፍየልና በግ የእንስሳት ሃብት ምርታማነትና ጤንነት ሙያተኞችን እያሰለጠነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ለምርቃት ለበቁት ሰልጣኝ ሙያተኞችም በእንስሳት እንክብካቤና አመጋገብ፣ በሽታ መከላከልና ጤና አጠባበቅ፣ ምርት ማቀነባበሪያና የገበያ ትስስር ትምህርት መሰጠቱን አስረድተዋል። በስልጠናውም የያቤሎ፣ ጂንካ፣ ባኮ፣ አዳሚቱሉ፣ የዓርባ ምንጭ ምርምር ማዕከላት፣ የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት እንዲሁም የግል እርሻ ሙያተኞች መሳተፋቸውን አስረድተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ስንዴን በኩታ ገጠም በማልማታችን ኑሯችን እየተሻሻለ መጥቷል-  አርሶ አደሮች 
Jun 22, 2026 275
አምቦ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ ስንዴን በኩታ ገጠም ማልማት ከጀመሩ ወዲህ ኑሯቸው እየተሻሻለ መምጣቱን በምዕራብ ሸዋ ዞን የወልመራ ወረዳ አርሶአደሮች ተናገሩ፡፡ በዞኑ ወልመራ ወረዳ የመኸር ኩታ ገጠም ስንዴ ልማት ዘር ማስጀመሪያ መርሃ ግብር የዞኑ እና የወረዳው የስራ ሀላፊዎች በተገኙበት ተካሄዷል፡፡ በወቅቱ ኢዜአ ያነጋገራቸው የወረዳው አርሶአደሮች ባለፉ ዓመታት ስንዴን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ ከአርሶ አደሮቹ መካከል ነገሰ ለታ እንደገለጹት ባለፉት ሶስት ዓመታት ከአካባቢው አርሶ አደሮች ጋር በመደራጀት በኩታ ገጠም ስንዴን እያለሙ ነው፡፡ ስንዴን በኩታ ገጠም ማልማታቸው ከዚህ በፊት ከአንድ ሄክታር ያገኙት የነበረውን 20 ኩንታል ምርት አሁን ላይ ወደ 40 ኩንታል ማድረስ እንደቻሉ ተናግረዋል። የስንዴን ምርታማነት ለማሳደግም ግብአትን በአግባቡ መጠቀምና ከወረዳው ግብርና ጽህፈት ቤት ባለሙያዎች ሙያዊ ድጋፍ ማግኘታቸውን ጠቁመዋል። ሌላው አርሶ አደር ደንደና ከበደ በበኩላቸው በመኸር እርሻ ከስንዴ ልማታቸው የተሻለ ምርት ለማግኘት በኩታ ገጠም ማረሳቸውን ተናግርዋል። የባለፉት አመታት የኩታገጠም እርሻ የተሻለ ምርት ለማግኘት እንደረዳቸው ጠቁመው ዘንድሮም ተግባሩን ለማስቀጠል እየተጉ መሆናቸውን ገልጸዋል ። ከአካባቢያቸው አርሶአደሮች ጋር በኩታ ገጠም ማረሳቸው ከኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው ባለፈ በማህበራዊ ኑሯቸው ላይም ለውጥ ማምጣቱን አስረድተዋል፡፡ የወረዳው ግብርና ጽፈት ቤት የግብርና ግብአት በወቅቱ ማቅረቡም ለምርታማነታቸው ማገዙን ጠቅሰዋል። የወልመራ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጋሪ በበኩላቸው፤ በወረዳው የአርሶአደሮችን ምርታማነት በማሳደግ ከተረጅነት ለማውጣት በቅንጅት መሰራቱን ጠቁመዋል። ለዚህም ለአርሶ አደሩ ግብአትና ሙያዊ ድጋፍን በማቅረብ በምግብ ራስን ከመቻል አልፎ የቁጣባ ባህሉ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በዘንድሮ መኸር እርሻ በወረዳው ከ34 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ከታቀደው ውስጥ 18 ሺህ ሄክታሩ በስንዴ እንደሚለማ ተናግረዋል። ከስንዴ ልማቱም 900 ሺህ ኩንታል ምርት ለማገኘት ታቅዶ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ መርጋ አየለ፤ በዞኑ በመኸር እርሻ ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለመሸፈን ታቅዷል ብለዋል። በመኸር አዝመራው በቆሎ፣ ማሽላ እና ስንዴ በኩታ ገጠም እንደሚለሙ ጠቁመው ከዚህም ውስጥ ከ232 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ ለማልማት መታቀዱን ተናግረዋል፡፡ መንግሥት ለግብርናው ዘርፍ በሰጠው ትኩረት የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ማሳድግ መቻሉን የገለጹት ደግም የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አበበ ጨመዳ ናቸው። የግብርናውን ውጤታማነት ለማሳደግ ለግብርና ቴክኖሎጂና ግብአት አቅርቦት ትኩረት መሰጠቱን አንስተዋል። የአርሶ አደሩን የኩታ ገጠም አስተራረስ ግንዛቤ በማጎልበት ምርታማነቱን በማሳድግ ከፍጆታው አልፎ ለገበያ የሚያቀርብበትን አቅም ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።
የመስኖ ፕሮጀክቶችን በጥራትና ፍጥነት በማጠናቀቅ የልማት አቅም ለማድረግ የስታንዳርድ አሰራሮች ስራ ላይ ውለዋል
Jun 22, 2026 614
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በጥራትና ፍጥነት በማጠናቀቅ የልማት አቅም ለማድረግ የሚያስችሉ የስታንዳርድ አሰራሮች ስራ ላይ ማዋሉን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ዴኤታ አብዱረህማን አብደላ ገለፁ። የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ከክልል መስኖ ቢሮ ኃላፊዎች ጋር በመሆን በውስጥ ስታንዳርድ ዝግጅትና ትግበራ ዙሪያ የልምድ ልውውጥ መድረክ አካሂዷል።   የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ዴኤታ አብዱረህማን አብደላ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፣ አዲሱ ስታንዳርድ እያንዳንዳቸው የመስኖ ፕሮጀክቶች የሚያልፉበትን ሂደት በግልጽ ያስቀምጣል። ስታንዳርዱ በፌደራል ደረጃ ብቻ ሳይሆን በክልሎችም በሚገነቡ አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶችን ጭምር ታሳቢ ያደረገ ነው ብለዋል። በትግበራው አማካኝነት ትልቁ የመስኖ ፕሮጀክቶች ፈተና የሆነው የዲዛይንና ጥናት ችግር ከስር መሰረቱ እንደሚፈታ ጠቁመዋል።   የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የመስኖ ፕሮጀክቶች ጥናትና ዲዛይን መሪ ሰራ አስፈፃሚ ያሬድ ሙላት፣ ሰነዱን ሙሉ በሙሉ በውስጥ አቅም የተዘጋጀ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ስታንዳርዱ ከህዳር 2017 ዓ.ም ጀምሮ ሙሉ በሙሉ ወደ ትግበራ መግባቱን አስታውቀዋል። በዚህም በመስኖ ፕሮጀክቶች ላይ ከዚህ ቀደም ይነሱ የነበሩ የጥራትና የዲዛይን ለውጥ ጥያቄዎች መስተካከሉን እና በርካታ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ወደ አገልግሎት መግባታቸውን ጠቅሰዋል፡፡   በመድረኩ አስተያየት የሰጡት የሲዳማ ክልል የመስኖ ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መስፍን በላይ ከዚህ ቀደም ጥናቶች በሚገባ ሳይጠናቀቁ ወደ ግንባታ በመገባቱ ፕሮጀክቶች ይጓተቱ እንደነበር አስታውሰዋል። የስታንዳርድ መዘጋጀት የትኛው ተግባር መቅደም እንዳለበት በግልጽ ስለሚያስቀምጥ ይህንን ክፍተት ሙሉ በሙሉ እንደቀረፈው ገልጸዋል።   የኦሮሚያ መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኢንጂነር አለሙ ረጋሳ በበኩላቸው አሰራሩ ሀገር በዘርፉ የያዘችውን ትልቅ የመስኖ ልማት እቅድ በጥሩ ሁኔታ ለማሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል።   የአፋር ክልል መስኖና ቆላማ ቢሮ ምክትል ሃላፊ ኢንጂነር መሐመድ ሁማድ አሁን ላይ ስታንዳርዱ በመዘጋጀቱና ስራዎች በህግና በስርዓት መመራት በመጀመራቸው፣ ቀደም ሲል በዘርፉ ይታይ የነበረውን ተግዳሮቶችን መድፈኑን ተናግረዋል።
ፋውንዴሽኑ ከመንግሥት ተቋማት ጋር በመቀናጀት ለስራ ፈጣሪ ወጣቶች ድጋፍ እያደረገ ነው
Jun 22, 2026 276
ጂንካ፤ሰኔ 15/2018(ኢዜአ) ፡-የኃይለማርያምና ሮማን ፋውንዴሽን ከመንግሥት ተቋማት ጋር በመቀናጀት በሚያደርግላቸው ድጋፍ ተጠቃሚ መሆናቸውን በደቡብ ኦሞ እና በአሪ ዞኖች የሚገኙ ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ተናገሩ። ፋውንዴሽኑ ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን እና ከመንግስታዊ ተቋማት ጋር በመቀናጀት በወጣቶች የኢኮኖሚ አቅም ግንባታ ላይ ያከናወናቸውን ተግባራት አስመልክቷል።   በጂንካ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው ኤግዚቢሽን ላይ ስራዎቻቸውን ያቀረቡ ስራ ፈጣሪ ወጣቶችም የኃይለማርያምና ሮማን ፋውንዴሽን ከመንግሥት ተቋማት ጋር በመቀናጀት በሚያደርጉላቸው ድጋፎች ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ገልጸዋል። በአሪ ዞን የደቡብ አሪ ወረዳ ነዋሪ ወጣት ያዕቆብ ገርሲኖ በፋውንዴሽኑ እና በመንግሥት ተቋማት ድጋፍ 10 አባላት ያሉት ማህበር በማቋቋም በንብ ማነብ ስራ እንደተሰማሩ ገልጿል። በአሪ ዞን ጂንካ ከተማ በዶሮ እርባታ ከተሰማሩ ወጣቶች መካከል ወጣት ወንድምነህ ሀብታሙ እንደገለፀው 10 አባላት ያለው ማህበር በማቋቋም በ45 ቀን ጫጩት አቅርቦት እና በዕንቁላል ጣይ ዶሮ እርባታ መሰማራታቸውን ጠቁሟል። ፋውንዴሽኑ እና መንግስታዊ ተቋማት ድጋፍ በዶሮ እርባታ በቂ ስልጠና መውሰዳቸውን ጠቁመው ፥ አሁን ላይ እስከ 4 ሺህ ጫጩቶችን ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ተናግሯል። ሌላው በደቡብ ኦሞ ዞን ሐመር ወረዳ ወጣት ሉቲየ ወንጌላ በበኩሉ 10 አባላት ያለው ማህበር በማቋቋም ፍየል በማሞከት ለገበያ የማቅረብ ስራ ላይ መሰማራታቸውን ገልጿል። በወሰዱት በቂ ስልጠናና እና ድጋፍ ፍየሎችን በማድለብና ለገበያ በማቅረብ የተሻለ ገቢ እያገኘ መሆኑንም ጠቁመዋል ።   የፋውንዴሽኑ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ ሶስና ኃይለማርያም (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለፁት የኃይለማርያም እና ሮማን ፋውንዴሽን ከመንግስታዊ ካልሆኑ ተቋማትና ከመንግስታዊ ተቋማት ጋር በመተባበር በደቡብ ኦሞ እና በአሪ ዞኖች በተመረጡ ወረዳዎች የወጣቶች የራስ ስራ ፈጠራ ፕሮጀክት ተግባራዊ እያደረገ ነው። የዚህ ፕሮጀክት ዓላማ ሥራ ፈላጊ ወጣቶችን በክህሎት ስልጠናዎች ማብቃት፣ ኢንተርፕራይዞችን እንዲያቋቁሙ መደገፍ፣ የፋይናንስ አቅርቦትን ማመቻቸት መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ እንዲሁም ቀጣይነት ያለው የገበያ ትስስርና ተቋማዊ ድጋፍ እንዲኖር በማስቻል መንግስት ለወጣቶች የስራ ዕድል ለማመቻቸት እና የወጣቶችን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት እያደረገ ያለውን ጥረት ማገዝ እንደሆነ ገልጸዋል። ላለፉት ሁለት ዓመታት በየደረጃው ከሚገኙ መንግስታዊ መዋቅሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት በሁለቱ ዞኖች 31 ሺህ 617 ወጣቶችን በንግድ ክህሎት ስልጠና በመስጠት የማብቃት ስራ መስራቱን አንስተዋል። የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ በበኩላቸው ፋውንዴሽኑን በዞኑ የሚገኙ ስራ ፈጣሪ ወጣቶችን የክህሎት እና የፋይናንስ አቅም በማጎልበት ትልቅ እገዛ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። መንግስት የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ሰፊ ርብርብ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው፥ የፋውንዴሽኑ ድጋፍም ወጣቶቹ ውጤታማ እንዲሆኑ አቅምን ይፈጥራል ብለዋል። የደቡብ ኦሞ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ታደለ ጋያ በበኩላቸው ፋውንዴሽኑ በአርብቶ አደሩ አካባቢ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመቅረፅ የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።   ፋውንዴሽኑ የወጣቶችን አቅም ከማጎልበት ባሻገር ተማሪዎችን የምገባ መርሃ ግብር በመደገፍ፣ ዘመናዊ እርሻን በማስተዋወቅ፣ በተፈጥሮ አያያዝና እንክብካቤ ረገድ ግንዛቤ በመፍጠር በጤናው ዘርፍ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል።  
አዲስ አበባ በኮሪደርና በወንዝ ዳርቻ ልማት እንደ አዲስ ነው የተወለደችው
Jun 22, 2026 229
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ በአጭር ጊዜ የተገነቡ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎች ከተማዋን አዘምነዋታል ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው በመዲናዋ የሚኖሩ የውጭ ሀገራት ዜጎች ገለጹ። አዲስ አበባ የህብረ ብሔራዊት ኢትዮጵያ ርዕሰ ከተማ፣ የአፍሪካ መዲና፣ የዓለም የዲፕሎማሲ ማዕከል እና የውጭ ዜጎችን ጨምሮ የብዙኃን መኖሪያና የጉብኝት ከተማ ናት። ይህች ታሪካዊ ከተማ ለወትሮው በአየር ንብረቷ እንጂ በመሰረተ ልማት ዝርጋታዋ በበጎ አትጠቀስም ነበር። ዛሬ ላይ ግን ያ ታሪክ ተቀይሯል። የለውጡ መንግሥት እንደ አዲስ መልሶ ከገነባቸው ታላላቅ ስኬቶች መካከል አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብ እና ፅዱ ያደረጋት የኮሪደር ልማት ግንባር ቀደሙን ስፍራ ይይዛል።   አዲስ አበባ የአፍሪካ መዲናነቷን ይበልጥ ለማስቀጠልና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለመሆን በሁሉን አቀፍ የለውጥ ጎዳና ላይ ትገኛለች። ዛሬ ከተማዋ ታሪካዊ ቅርሶቿን ጠብቃ፣ የነዋሪዎቿን የኑሮ ጥራት ባሻሻለ እና የውጭ ዜጎችን ቀልብ በሳበ መልኩ የዘመናዊነት ማማ እየሆነች ነው። ይህ የመዲናዋ ፈጣን ለውጥ በብዙ የዓለም መሪዎችና በአፍሪካውያን ዘንድ ከፍተኛ አድናቆት እየተቸረው ይገኛል። በተለይም በከተማዋ በተለያዩ የሥራ መስኮች ተሰማርተው የሚኖሩ የውጭ ሀገራት ዜጎች የአዲስ አበባን ዕድገትና የዝማኔ ጉዞ በዓይናቸው እያዩት፣ በፈጣን ጊዜ ውስጥ የተሳካ መሆኑ እያስደነቃቸው ነው። ለወትሮው ይመለከቷቸው የነበሩት ጎስቋላ ሰፈሮች፣ የተቆፋፈሩና ለእግረኛ የማይመቹ መንገዶች ዛሬ እጅግ ዘምነዋል። ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የከተማ መዝናኛ፣ መኖሪያና የሥራ ከባቢም ተፈጥሯል። በአዲስ አበባ በሚኖሩትና በኢፌዲሪ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት በአይሲቲ የትምህርት ክፍል መምህር የሆኑት ህንዳዊው ፕሮፌሰር ራቪንድራ ባቡ፣ የከተማዋን ለውጥ ማመን ነው ያቃተኝ፤ ልክ እንደ አዲስ ነው የተወለደችው ሲሉ ነው የገለጹት።   አዲስ አበባን ከለውጥ በፊት፣ የለውጥ ሂደቱንና ከለውጥ በኋላ በአግባቡ እንደተመለከቷት ጠቅሰው፤ በፊት ከሚያውቋት ፍጹም በተለየ መልኩ ወደ ከፍተኛ የዕድገት ጎዳና ተሻግራ በማየታቸው መደነቃቸውን ይናገራሉ። የከተማዋን ገጽታ የሚያስውቡና ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያላቸው የመሠረተ ልማት ሥራዎች በስፋት መገንባታቸው ለከተማዋ መዘመን ጉልህ አበርክቶ እንዳለው ነው ያነሱት ፕሮፌሰሩ። ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ጸጋ የታደለች እና ምቹ የሆነ የአየር ጸባይ ያላት ሀገር መሆኗንም ይመሰክራሉ። በአዲስ አበባ ነዋሪ የሆኑትና በኢፌዲሪ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት የኮንፊሽየስ ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር የሆኑት ቻይናዊው ፓን ሊያንግ፤ የአዲስ አበባ ዕድገት ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀ የዘመናዊነት ጉዞ ነው ይላሉ። የከተማዋ የተቀናጀ የመሠረተ ልማት ዝርጋታ ሲከናወን በቅርበት መመልከታቸውን ጠቅሰው፤ የወንዝ ዳርቻና ሌሎች የልማት ሥራዎች ከተማዋ ውብ እንድትሆን እያደረጓት መሆኑን ይናገራሉ። አዲስ አበባ በአጭር ዓመታት ያስመዘገበችው ስኬትም የአፍሪካ የዘመናዊነት መሠረትና የፈጣን ልማት ምሳሌ መሆኑን ጠቅሰዋል።   የአዲስ አበባን ገጽታ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከቀየሩ ሜጋ ፕሮጀክቶች መካከል የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት ሰፊ የእግረኛ መንገዶች፣ የብስክሌት መንገዶችን፣ አረንጓዴ ስፍራዎችንና ዘመናዊ የመንገድ መብራቶችን፣ ደረጃቸውን የጠበቁ የመኖሪያና የንግድ ስፍራዎችን በማካተት መዲናዋን ወደ ዓለም አቀፍ የዝማኔ ደረጃ አሳድጓታል። የወንዝ ዳርቻ ልማትም ቀደም ሲል በቆሻሻ የተበከሉ የወንዝ ዳርቻዎችን ወደ ውብ የሕዝብ መዝናኛነት የቀየረ ግዙፍ ፕሮጀክት ነው። ፕሮፌሰር ራቪንድራ ባቡ እና ፓንሊያንግ እንደሚመሰክሩት የከተማዋ አየር ንብረትና መልክዓ-ምድር ተስማሚ በመሆኑ፣ ከኮሪደርና ከአረንጓዴ ልማት ጋር ተዳምሮ ለቱሪዝምና ለኑሮ እጅግ ተመራጭ አድርጓታል።
የመስኖ መሰረተ ልማት ውጤታማነት የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ስኬታማ ጉዞ እየገነባ ነው
Jun 22, 2026 138
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦የመስኖ መሰረተ ልማት ውጤታማነት በግብርና ዘርፍ የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ስኬታማ ጉዞ እየገነባ መሆኑን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ዴኤታ አብዱረህማን አብደላ ገለጹ። የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ከክልል መስኖ ቢሮ ኃላፊዎች ጋር በመሆን በውስጥ ስታንዳርድ ዝግጅትና ትግበራ ዙሪያ የልምድ ልውውጥ መድረክ እያካሄደ ይገኛል። የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ዴኤታ አብዱረህማን አብደላ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በጥራትና ፍጥነት በማጠናቀቅ የልማት አቅም እንዲሆኑ እየተደረገ ነው። የመስኖ መሰረተ ልማት ውጤታማነትን ለማሻሻልም በስታንዳርድ መምራት የሚያስችሉ በርካታ የአሰራር ሥርዓቶች ተዘጋጅተው ስራ ላይ እንዲውሉ መደረጉን ገልጸዋል። የስታንዳርድ የአሰራር ሥርዓቶችም በፌደራልና የክልል መንግሥታት የሚከናወኑ የመስኖ ልማት ሥራዎችን በተደራጀ መልኩ እንዲመሩ በማስቻል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በሀገር አቀፍ ደረጃ በተቀናጀ አግባብ የሚከናወኑ የመሰረተ ልማት ሥራዎች የመስኖ ልማት ሽፋንን በማሳደግ በምርታማነት ዕድገት ላይ ወሳኝ ሚና እየተወጡ ነው ብለዋል። በመስኖ መሰረተ ልማት ውጤታማነትም የበጋ መስኖ ስንዴን ጨምሮ በሁሉም ዘርፍ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ አስደናቂ ውጤት እየተገኘ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም ከውጭ የሚገቡ የግብርና ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የምግብ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥ ስኬታማ ጉዞን እያፋጠነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የግብርና ልማት ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ በሁሉም ወቅቶች የማምረት ስራ ባህል ሆኖ እንዲቀጥል በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
ብልጽግና ፓርቲ ህዝብ የሰጠውን ኃላፊነት በመወጣት የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ማስቀጠል ይጠበቅበታል
Jun 22, 2026 202
አሶሳ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ ብልጽግና ፓርቲ ሕዝብ የሰጠውን አደራና ኃላፊነት በመወጣት፣ የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል እንዳለበት የአሶሳ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ትናንት ባስታወቀው መሠረት ብልጽግና ፓርቲ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ አብላጫ የምክር ቤት መቀመጫዎችን በማግኘት አሸንፏል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የአሶሳ ከተማ ነዋሪዎች፤ አሸናፊው ብልጽግና ፓርቲ ተጨማሪ የህዝብ አደራን በመቀበል ለቀጣይ አምስት ዓመታት መሠረታዊ የልማት ስራዎችን ለማከናወን የሚያስችለውን ዕድል አግኝቷል። ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ አልሃጂ ሀሊፋ እንደተናገሩት፤ የምርጫው ውጤት ብልጽግና ፓርቲ እያከናወናቸው የሚገኙ ትላልቅ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ የተሻለች ሀገር ለመገንባት በሚደረገው ሂደት አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል። ፓርቲው የህዝቡን ይሁንታ ያገኘ በመሆኑ ከህዝቡ የሚነሱ የልማት፣ የመልካም አስተዳደርና ሰላም የማስከበር ጥያቄዎችን ለመመለስ ከመቼውም ጊዜ በላይ ዝግጁ መሆን እንዳለበትም ገልጸዋል። ሌላው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ጉዴታ ነጋሳ በበኩላቸው፤ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሁሉም መስክ ስኬታማ መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም በህዝብ ተወካዮች እና በክልል ምክርቤቶች ተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎችም ከዚህ በፊት ከነበረው የተሻለ መቀመጫ ማግኘታቸው የፖለቲካ ምህዳሩ እየሰፋ መምጣቱን ያሳያል ብለዋል። አሸናፊው ብልጽግና ፓርቲም ያገኘውን ዕድል በመጠቀም በሁሉም አካባቢዎች አስተማማኝ ሰላም እንዲሰፍን እና የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ትልቅ የቤት ስራ እንደሚጠብቀው ተናግረዋል። የምርጫው ውጤት የኢትዮጵያን አሸናፊነት ያረጋገጠ እና የህዝብ ድምጽ ምን ያክል ዋጋ እንዳለው ያስመሰከረበት ነው ያሉት ደግሞ የከተማዋ ነዋሪ አቶ አደም ሳለህ ናቸው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫ ሂደቱን ነፃ እና ገለልተኛ ሆኖ ያከናወነበት ሁኔታ የሚደነቅ መሆኑን በመጥቀስ። በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለሕዝብ ተወካዮች እና ለክልል ምክር ቤቶች ብልጽግና ፓርቲ አብላጫ የምክር ቤት መቀመጫ በማግኘት ማሸነፉን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ትናንት ይፋ ማድረጉ የሚታወስ ነው። የምርጫው ውጤት ይፋ መደረጉን ተከትሎም ብልጽግና ፓርቲ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ምስጋና ያቀረበ ሲሆን፤ ፓርቲው በቅድመ ምርጫ ለህዝብ የገባውን ቃል ሳይሸራረፍ በመተግበር ሕዝብን በቅንነትና በታማኝነት እንደሚያገለግልም አረጋግጧል።
የክልሉን የገቢ አቅም በማሳደግ የልማትና የመልካም አስተዳደር እቅዶችን ለማሳካት ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 22, 2026 116
ጋምቤላ ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል የገቢ አቅምን በማሳደግ የልማትና የመልካም አስተዳደር እቅዶችን ለማሳካት ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ። በክልሉ የገቢ እቅድ አተገባበር ዙሪያ የገቢ ሰብሳቢ ተቋማት አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት የውይይት መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተካሂዷል።   የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ኡማን አሙሉ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ ክልሉ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የታለሙትን የልማትና የመልካም አስተዳደር እቅዶች ለማሳካት ትኩረት ተሰጥቷል። ለእቅዱ ስኬታማነት የዘርፉ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ቁርጠኝነት የላቀ ድርሻ ያለው መሆኑን አስገንዝበዋል። የግብር አሰባሰብ ሂደቱ ፍትሃዊ፣ ግልጽና ዘመናዊ አሰራርን የተከተለ እንዲሆን በትጋት እንደሚሰራ አመላክተዋል።   የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ ቸንኮት ዴቪድ በበኩላቸው፤ በክልሉ ያለውን የገቢ አቅም በአግባቡ ለመሰብሰብና ለመጠቀም አዳዲስ አሰራሮች ተግባራዊ እየተደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። የውይይት መድረኩ ዋና ዓላማም በአዳዲስ አሰራሮች ላይ የሚመለከታቸው አካላት በቂ ግንዛቤ ይዘው እንዲሰሩ ማስቻል መሆኑን አስታውቀዋል። በክልሉ ባለፉት 11 ወራት ከ4 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡ ተመላክቷል።
የተጀመሩ የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ የምናደርገውን ተሳትፎ አጠናክረን እንቀጥላለን-ወጣቶች
Jun 22, 2026 151
አምቦ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ከአሸናፊው ፓርቲ ጎን በመቆም የአካባቢያችንን ሰላም በመጠበቅ የተጀመሩ የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ የምናደርገውን ተሳትፎ አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ የአምቦ ከተማ ወጣቶች ገለጹ። በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለሕዝብ ተወካዮች እና ለክልል ምክር ቤቶች ብልጽግና ፓርቲ አብላጫውን መቀመጫ በማግኘት ማሸነፉን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የአምቦ ከተማ ወጣቶች፤ የአካባቢያቸውን ሰላም በመጠበቅ የተጀመሩ የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ ከአሸናፊው ፓርቲ ጎን በመሆን የሚያደርጉትን ተሳትፎ እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወጣት ሽብሩ ነገሪ፤ ብልጽግና ፓርቲ የሕዝቡን ጥያቄ መፍታት የሚችሉና ቀደም ሲል በሀገርና በክልል ደረጃ የተጀመሩ ታላላቅ ፕሮጀክቶችን አጠናክሮ ማስቀጠል አለበት ብሏል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የታቀዱ ግዙፍ የልማት ስራዎች እንዲሳኩ ከፓርቲው ጎን በመሆን የበኩሉን እንደሚወጣ ገልጿል። በከተማዋ በሁሉም ዘርፎች እየተካሄዱ ያሉ የልማት ሥራዎችን ለማገዝ መዘጋጀቱን የገለጸው ደግሞ ወጣት ዮሐንስ ሚደቅሳ ነው። ከአሸናፊው ፓርቲ ጋር በመሆን በተጀመሩ የልማት ሥራዎች ላይ በመሳተፍ እንዲሁም የአካባቢውን ወጣቶች በማስተባበር የሚጠበቅበትን ሚና ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን ገልጿል። ወጣት ጭምዴሳ ነገሪ በበኩሉ፤ አብላጫ የምክርቤት መቀመጫ ያገኘው ፓርቲ ከዚህ ቀደም ዜጎች ሲያነሷቸው የነበሩ የልማት ጥያቄዎችን መመለስ ይጠበቅበታል ብሏል። የተጀመሩና የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ፕሮጀክቶች እንዲቀጥሉ የበኩሉን እንደሚወጣም ገልጿል።
በሀገሪቱ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ማስቀጠልና ማጠናቀቅ፣ ከብልጽግና ፓርቲ የሚጠበቅ ታሪካዊ ኃላፊነት ነው
Jun 22, 2026 120
ጅግጅጋ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በሀገሪቱ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ማስቀጠልና ማጠናቀቅ፣ ከብልጽግና ፓርቲ የሚጠበቅ ታሪካዊ ኃላፊነት ነው ሲሉ የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሕዝብ ተወካዮች እና የክልል ምክር ቤቶች ብልጽግና ፓርቲ አብላጫውን መቀመጫ በማግኘት ማሸነፉን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል። የምርጫውን ውጤት ይፋ መሆን በማስመልከት ኢዜአ ያነጋገራቸው የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች፤ ብልጽግና ፓርቲ የሕዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል እንዳለበት ገልጸዋል። ነዋሪዎቹ አክለውም፤ ለሀገሪቱ ዕድገትና ልማት መጎልበት ሕዝቡም ከፓርቲው ጎን በመቆም የድርሻውን ማበርከት እንዳለበት ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ አደን ዩሱፍ እንደተናገሩት፤ በተለያዩ ዘርፎች የተመዘገቡትን የለውጥ ውጤቶች ማስቀጠል የአሸናፊው ፓርቲ ሃላፊነት ነው። ለውጦቹን በመደገፍም ለሀገራቸው ልማት የበኩላቸውን ኃላፊነት ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሌላኛው ነዋሪ አቶ መሀመድ አብዲ በበኩላቸው፤ መንግሥት ባለፉት አምስት ዓመታት ሲያከናውናቸው የነበሩ የልማት ሥራዎችን የበለጠ ማጠናከር እንዳለበት ገልጸዋል። በተለይም በግብርናው ዘርፍ የተሰጠው ትኩረት የምግብ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥና በምግብ ራስን ለመቻል የሚያስችል በመሆኑ፣ በቀጣይም ለዘርፉ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አሳስበዋል። ፓርቲው በውኃ ተደራሽነት፣ በከተሞች መሠረተ-ልማት ማስፋፋትና የኑሮ ውድነትን በመቀነስ ረገድም የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማዕከል አድርጎ መሥራት እንዳለበት አክለው ገልጸዋል። በሀገሪቱ የተጀመሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተጠናቀው ለአገልግሎትና ለምርታማነት እንዲበቁ በትኩረት መሥራት እንደሚያስፈልግ የገለጸው ደግሞ ወጣት አህመድ ኢብራሂም ነው። የመንግሥት ሠራተኞችን ተጠቃሚነት ማሳደግና የተለያዩ ሥልጠናዎችን በመስጠት አቅማቸውን በማጎልበት፣ የአገልግሎት አሰጣጥን ማሻሻል እንደሚገባም ገልጿል። ነዋሪዎቹ የመንግሥትን የልማት ጥረቶች በመደገፍና የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ በማድረግ ረገድ የበኩላቸውን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል። የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የመጨረሻ ውጤት ይፋ መሆኑን ተከትሎ አሸናፊ የሆነው ብልፅግና ፓርቲ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ ምስጋና አቅርቧል። በመልእክቱም በአጠቃላይ ብልፅግና ፓርቲ የገባውን ቃል ሳይሸራረፍ በመተግበር፣ ምርጫ የሥልጣን መቆናጠጫ ሳይሆን ሕዝብን በቅንነትና በታማኝነት ማገልገያ ታላቅ አደራ መሆኑን ገልጿል። በመሆኑም የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልፅግና በተግባር የማረጋገጥ ታሪካዊ ጉዟችንን ከምንጊዜውም በላይ በበለጠ ትጋት፣ አንድነትና ቁርጠኝነት አጠናክረን ለመቀጠል ለተከበረው ሕዝባችን ዳግም ቃላችንን እናድሳለን ሲል ማረጋገጡ ይታወሳል።
ብልጽግና ፓርቲ አብላጫ የምክር ቤቶች መቀመጫ በማግኘት አሸናፊ መሆኑ የተጀመሩ ሁለንተናዊ የልማት ሥራዎችን ለስኬት ለማብቃት ዕድል ይፈጥራል
Jun 22, 2026 122
ወልቂጤ፤ ሰኔ 15/2018 (ኢዜአ)፦ብልጽግና ፓርቲ አብላጫ የምክር ቤቶች መቀመጫ በማግኘት አሸናፊ መሆኑ የተጀመሩ ሁለንተናዊ የልማት ሥራዎችን ለስኬት ለማብቃት ዕድል ይፈጥራል ሲሉ የወልቂጤ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ። በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ብልጽግና ፓርቲ መንግስት ለመመስረት የሚያስችለውን አብላጫ የምክር ቤት መቀመጫ ማግኘቱን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ትናንት ይፋ ማድረጉ የሚታወስ ነው። በእዚህም ፓርቲው ለሕዝብ ተወካዮች እና ለክልል ምክር ቤቶች አብላጫውን መቀመጫ በማግኘት ማሸነፉን አስታውቋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫውን ውጤት ይፋ ማድረጉን ተከትሎ የኢዜአ ሪፖርተር በወልቂጤ ከተማ ነዋሪዎችን አነጋግሯል። ነዋሪዎቹ ፤ በምርጫው ከጅምሩ እስከመጨረሻው የታየው ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሂደት በሀገሪቱ የዴሞክራሲ ሥርአት ጥሩ መሰረት እየያዘ መምጣቱን ያመላከተ ነው ብለዋል። በምርጫው ቀን ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ለመጠቀም ከማለዳ እስከ እኩለሌሊት ረጃጅም ሰልፎችን ታግሰው ድምጽ እንደሰጡ አስታውሰው፣ በዚህም ደስተኞች መሆናቸውን ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አቶ ሀይሉ ተሰማ፣ ወይዘሪት ሳድያ ኑረዲን እና አቶ መንግስቱ ባንቀስራ፤ በምርጫው ብልጽግና ፓርቲ አብላጫ የምክር ቤት መቀመጫ በማግኘት አሸናፊ መሆኑ ባለፉት ዓመታት የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን ለስኬት ለማብቃት መልካም እድል መሆኑን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት በብልጽግና ፓርቲ የተመራው መንግስት ያከናወናቸው የልማት ሥራዎች ለኢትዮጵያ እድገትና ማንሰራራት መሰረት ያኖሩ መሆኑን አንስተው በቀጣይ ለላቀ ስኬት መትጋት እንዳለበት ተናግረዋል። በተለይም የተጀመሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች እንዲሳኩ፣ የከተሞችና የገጠር ኮሪደር ልማት ቀጣይነት እንዲኖረው እንዲሁም ለግብርና ምርታማነት ማደግ ብዙ መስራት አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም ለሀገር ልማት ስኬትና እድገት የመንግስት ጥረት ብቻውን በቂ ባለመሆኑ የበኩላችንን አስተዋጽኦ ለማድረግ ተዘጋጅተናል ብለዋል። የኢትዮጵያን ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና እድገት እውን ለማድረግ ከመንግስት ጋር በተደመረ አቅምና በተባበረ ክንድ መስራት ይኖርብናል ሲሉም ነዋሪዎቹ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ቀጣናዊ ሰላምና ዕድገትን ከማረጋገጥ የሚመነጭ ምክንያታዊ አጀንዳ ነው
Jun 21, 2026 694
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 14/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሕጋዊና ታሪካዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ቀጣናዊ ሰላምና ዕድገትን ከማረጋገጥ የሚመነጭ ምክንያታዊ ወሳኝ አጀንዳ መሆኑን ምሁራን ገለጹ። የኢትዮጵያ ረጅሙ የስልጣኔ ታሪክና ሃያልነት ከተፈጥሯዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጋር በእጅጉ የተቆራኘ መሆኑን የታሪክ ድርሳናት ከትበው ያስቀመጡት የአደባባይ ሃቅ ነው። የሀገር ውስጥ ባንዳና የውጭ ባዕዳን ታሪካዊ ጠላቶች የሸረቡት ሴራም የኢትዮጵያን ተፈጥሯዊ የባሕር በር ባለቤትነት በማሳጣት በሀገር ላይ ኢ-ፍትሐዊ በደል ተፈጽሟል። በኢትዮጵያዊያን ልብ ለሶስት አስርት ዓመታት ተዳፍኖ እንዳይነሳ ተደርጎ የቆየው የባሕር በር ባለቤትነትም በሀገራዊ ለውጡ ማግስት ወሳኝ አጀንዳ ሆኖ ቀርቧል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነትም ከፍተኛ የህዝብ ቁጥርን ከፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት አጣምሮ ለያዘ ሀገር ምላሽን የሚሻ ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ ፍትሐዊ፣ መልክዓምድራዊና ምክንያታዊ ጥያቄ ነው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ምሁራን፤ ኢትዮጵያ ከተፈጥሯዊና ሕጋዊ የባሕር በር ባለቤትነቷ እንድትገለል የተደረገበት አጋጣሚ የሚያስቆጭ መሆኑን ገልጸዋል።   በዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ የሥነ-አመራርና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር ጌትዬ ትርፌ(ዶ/ር)፤ የታሪካዊ ጠላቶችና የውስጥ ባንዳዎች የሴራ ጥምረት የባሕር በር ባለቤትነታችንን እንድናጣ አድርጓል ብለዋል። የግል ጥቅምን ከማስቀደም የተሻገር ርዕይ ያልነበረው የስልጣን ጥመኛ ቡድን የፈጸመው ክህደት የትውልድን ብሔራዊ ጥቅም አሳልፎ በመስጠት በሀገር ላይ ታሪክ ይቅር የማይለው በደል መፈጸሙን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያ ከባሕር በር ባለቤትነቷ በግፍ መነጠሏም፤ በገቢና ወጪ ዓለም አቀፍ የንግድ ተወዳዳሪነትን ከማቀጨጭ ባሻገር ቀጣናውን የሽብርተኞች መፈንጫ ማድረጉን ገልጸዋል። ከሀገራዊ ለውጡ በፊትም ለሶስት አስርት ዓመታት ታሪካዊ፣ ሕጋዊና መልክ ዓምድራዊ ይዞታዋ በአጀንዳነት እንዳይነሳ የተደረገበት ትርክትም ዜጎችን አሳዝኖ የቆየ እንደነበር አስረድተዋል። በሀገራዊ ለውጡ ማግስት ኢትዮጵያዊያን የጋራ አቋም በመያዝ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን በስትራቴጂክ ብሔራዊ ጥቅም አጀንዳነት ማቅረባቸው የታሪክ ስብራትን የማረም ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ዓለም አቀፍ ዕውቅናን እያገኘ የመጣ የስትራቴጂክ ብሔራዊ ጥቅም ማዕከል መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነትም ቀጣናዊ ትብብርና ጥንካሬን በማጎልበት የሰላም፣ የኢኮኖሚ ዕድገትና የገበያ ትስስር መሰረት መሆኑን አብራረተዋል።   በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር የፖሊሲና ስትራቴጂ ተመራማሪ ተመስገን ዋለልኝ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የባህር በር ለኢትዮጵያ ቅንጦት ሳይሆን የህልውና ጉዳይ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ከስትራቴጂክ የባሕር በር ባለቤትነት መገለሏ ሶስት አስርት ዓመታትን በተሻገረ ዘመን በዜጎች ህይወት ላይ ተፅዕኖ በማሳደር የሎጂስቲክስ ሥርዓት ላይ ከፍተኛ ጫና ማሳደሩን አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅትም የሃያላኑ ዐይን ማረፊያ በሆነው የቀይ ባሕር ቀጣና ኢትዮጵያዊያን ታሪካዊና ሕጋዊ የባሕር በር ባለቤትነታቸውን ለማስመለስ የሚያደርጉት ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስገንዝበዋል።
የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማትና የማስፋፊያ ሥራዎች በርካታ ዜጎችን የሀይል ተጠቃሚ አድርገዋል
Jun 21, 2026 471
ሀዋሳ፤ ሰኔ 14/2018(ኢዜአ):-የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት እና ተደራሽነትን በማስፋፋት የዜጎችን የሀይል ፍላጎት ለመመለስ በተከናወኑ ተግባራት በርካቶች ተጠቃሚ መሆናቸውን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። በሲዳማ ክልል ሆኮ ወረዳ ከጸሐይ ሀይል 525 ኪሎ ዋት ሀይል የሚያመነጭ ፕሮጀክት ተመርቋል።   የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደገለጹት ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ዜጎችን በኤሌክትሪክ ሀይል ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት ተከናውነዋል። ባለፉት ዓመታት የተለያዩ አማራጮች በመጠቀም የኤሌክትሪክ ሀይል መሰረተ ልማት እና ተደራሽነትን በማስፋፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ያስቻሉ ሥራዎች መከናወናቸውን አስታውሰዋል። በየዓመቱ ከዋናው የኤሌትሪክ ሀይል የሚጠቀሙ ሰዎችን ቁጥር ማሳደግን ጨምሮ አማራጭ ታዳሽ ሀይልን ለኤሌክትሪክ ሀይል ፍላጎት ለመጠቀም የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን ለማስፋፋት በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማትና ተደራሽነትን በማስፋፋት እያደገ የመጣውን የሀይል ተጠቃሚነት ፍላጎት ለመመለስ በተደረጉ ጥረቶች በርካቶች ተጠቃሚ መሆናቸውንም ሚኒስትር ዴኤታው አስረድተዋል። ለእዚህም ቀደም ሲል ከዋናው የኤሌክትሪክ ሀይል ተጠቃሚዎች ቁጥር በዓመት 240 ሺህ እንደነበር አስታውሰው በአሁኑ ወቅት ከ600 ሺህ በላይ ማድረስ መቻሉን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ባለፉት አራት ዓመታት ከ85 ሺህ በላይ የቤተሰብ ሶላርን ማሰራጨት ተችሏል ያሉት ኢንጂነር ሱልጣን (ዶ/ር)፣ ከ2 ሺህ በላይ ትምህርት ቤቶችና የጤና ተቋማትንም ተጠቃሚ በማድረግ የዜጎችን የማህበራዊ አገልግሎት ያሻሻሉ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል። በተጨማሪ በቤተሰብና በተቋማት ደረጃ የኢነርጂ ቆጣቢና ባዮ ማስ ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት በርካታ ዜጎች ተጠቃሚ ሆነዋል ብለዋል። በቀጣይም የኤሌክትሪክ ሀይል ተደራሽነትን ሽፋንን ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎችን በማጠናከር የተያዘውን ግብ ለማሳካት እንደሚሰራ አስታውቀዋል። በሀገሪቱ ፍትሀዊ የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲኖር በዋና መስመርና ከዋና መሰመር ርቀው የሚገኙ አካባቢዎችን ያካተተ ሥራ እየተሰራ ነው ያሉት ደግሞ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የፕሮጀክት ፖርትፖሊዮ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ክንፈ ነጋሽ ናቸው።   እሳቸው እንዳሉት በተለይም ከዋናው መስመር ርቀው የሚገኙ ገጠራማ አካባቢዎችን እንደ ሶላር ያሉ አማራጭ የታዳሽ ሀይል በመጠቀም የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። በዚህም እንደ ሀገር 97 ፕሮጀክቶች በግንባታ ላይ መሆናቸውን ጠቁመው፣ እስካሁን ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት በበቁ 43 ፕሮጀክቶች በርካታ ዜጎች ተጠቃሚ ሆነዋል ብለዋል። የኤሌክትሪክ ሀይል መስፋፋት ማህበራዊ አገልግሎቶችን ለማሳደግንና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴን ለማነቃቃት ጉልህ ሚና እንዳለው የተናገሩት ደግሞ የሲዳማ ክልል ማዕድንና ኢነርጂ ልማት ቢሮ ሃላፊ ኢንጂነር ከበደ ጋኖሌ ናቸው።   በክልሉም በመደበኛና በአማራጭ ታዳሽ ሀይል በርካታ ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረጉ ፕሮጀክቶች ተከናውነዋል ብለዋል። አስተያየታቸውን የሰጡት በሆኮ ወረዳ የሆዲ ቦኩ ከተማ ነዋሪዎች መካከል አቶ አለሙ ሎጊታ በበኩላቸው በመብራት እጦት በጨለማ ይኖሩ እንደነበር አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት የኤሌክትሪክ ሀይል ተጠቃሚ በመሆናቸው ችግራቸው መፈታቱን ተናግረዋል።   በአካባቢያቸው የኤሌክትሪል ሀይል ተደራሽ መሆኑን ተከትሎ የጤናና የትምህርት አገልግሎትን በአግባቡ እያገኙ መሆናቸውንም ተናግረዋል።    
በጅግጅጋ ከተማ የተገነቡ የኮሪደር ልማት ሥራዎች የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ናቸው
Jun 21, 2026 453
ጅግጅጋ፤ ሰኔ 14/2018(ኢዜአ)፦ በጅግጅጋ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር ልማት ስራዎች የከተማዋን ገጽታ በከፍተኛ ደረጃ በመቀየር የአካባቢውን ማኅበረሰብ ተጠቃሚ ማድረጋቸውን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ ። የኮሪደር ልማት በኢትዮጵያ ዋና ዋና ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ፣ ለኢንቨስትመንት ሳቢ እና የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ ታቅዶ በሀገር አቀፍ ደረጃ በልዩ ትኩረት እየተተገበረ የሚገኝ ዘመናዊ የከተማ ልማት ስትራቴጂ ነው።   ይህ መርሃ ግብር የመንገዶችን ስፋትና ጥራት ማሻሻልን፣ የባቡርና የእግር ማቋረጫዎችን፣ የብስክሌት መንገዶችን፣ አረንጓዴ ስፍራዎችንና የሌሊት መብራቶችን ማካተትን ታሳቢ ያደረገ ነው። የሶማሌ ክልል ርዕሰ መዲና የሆነችው ጅግጅጋ፣ ከሀገር ውስጥ አልፎ ለቀጣናዊ የንግድና የኮሪደር ትስስር ያላት ስትራቴጂካዊ መገኛ እጅግ ከፍተኛ ነው። በመሆኑም በከተማዋ የተጀመረው የኮሪደር ልማት የጅግጅጋን መሠረተ ልማት በማዘመንና የንግድ እንቅስቃሴን በማቀላጠፍ ረገድ የጎላ ድርሻ አለው። ይህ የልማት እንቅስቃሴ የከተማዋን ገጽታ ደረጃ በደረጃ በመቀየር ላይ የሚገኝ ሲሆን፣ ከውበት ባለፈም ለከተማዋ ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር፣ የንግድ አካባቢዎችን በማዘመን እና የሕዝብ መዝናኛ ስፍራዎችን በመጨመር የነዋሪዎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑ ይገለጻል።   የጅግጅጋ ከተማን የኮሪደር ልማት በማስመልከት ኢዜአ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች እንደገለጹት፤ የተከናወነው የልማት ሥራ የከተማዋን ገጽታ ከመለወጡ ባለፈ የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት አረጋግጧል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል የፋፈን ዞን የሀገር ሽማግሌ ሱልጣን በደል አሌሊ እንደገለጹት፤ የኮሪደር ልማቱ በተከናወነባቸው መንገዶች ላይ ጤናማ የእግር ጉዞ ለማድረግና በቀላሉ ለመዝናናት ተችሏል። በከተማዋ በኮሪደር ልማቱ የተገነቡት ፓርኮች ለጅግጅጋ ከተማ ተጨማሪ ውበትና ማራኪ ገጽታን የፈጠሩ መሆናቸውንም ተናግረዋል። የተገነቡት መሠረተ ልማቶች ወጣቶች ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ፣ ከአልባሌ ቦታዎች እንዲርቁና ለጤናቸው ተስማሚ የሆኑ እንቅስቃሴዎችን እንዲያደርጉ በማገዝ ረገድም የጎላ ሚና እንዳላቸው አስገንዝበዋል።   ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ሱልጣን አላሌ በበኩላቸው፤ በከተማዋ የተከናወኑት የኮሪደር ልማት ሥራዎች የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ መሆናቸውን ገልጸው፣ የተገነቡት የመዝናኛ ሥፍራዎችም ነዋሪዎች በቀላሉ እንዲንቀሳቀሱና እንዲዝናኑ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። የጅግጅጋ ከተማ የኮሪደር ልማት ከአካባቢው ማኅበረሰብ ባለፈ፣ የጎረቤት ሀገራት ነዋሪዎችንም የሚስብ ቀጣናዊ የመዳረሻ ማዕከል እያደረጋት መሆኑን አስገንዝበዋል። በጅግጅጋ ከተማ የተገነቡት የኮሪደር ልማት መሠረተ ልማቶች የከተማዋን ገጽታ በከፍተኛ ደረጃ የለወጡና ያሳመሩ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ አቶ መሐሙድ አሕመድ አብዲ ናቸው።   በአሁኑ ወቅት በክልሉ የተገኘውን ሰላምና ልማት አጠናክሮ በመቀጠል፣ የልማት ሥራዎችን ይበልጥ ማስፋፋትና መደገፍ እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል። የጅግጅጋ ከተማ ከንቲባ ኢንጂነር ሻፊ አሕመድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኮሪደር ልማቱ በከተማዋ ከፍተኛ መነቃቃትን በመፍጠር፣ የከተማነት ደረጃዋን ከፍ ያደረገ፣ ገጽታዋን የለወጠ እንዲሁም ጽዱና ውብ እንድትሆን ያስቻለ ነው።   የኮሪደር ልማቱ በክልል ደረጃ በጅግጅጋ ከተማ ተጀምሮ ወደ ሌሎችም ከተሞች እየሰፋ መሆኑን ጠቅሰው፤ መርሃ ግብሩ የኅብረተሰቡ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ፣ ለከተማዋ ውበትና ዕድገትም ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ታስቦ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።  
በሸገር ከተማ በመኸር እርሻ እስካሁን ከ89 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ታርሶ ለዘር ተዘጋጅቷል
Jun 21, 2026 389
ሸገር ፤ሰኔ 14/2018 (ኢዜአ)፡- በሸገር ከተማ በዘንድሮው የመኸር እርሻ በእስካሁኑ እንቅስቃሴ 89 ሺህ ሄክታር መሬት ታርሶ ለዘር መዘጋጀቱን የከተማ አስተዳደሩ የግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የሸገር ከተማ አስተዳደር በኢንዱስትሪና በከተማ ልማት ላይ ብቻ ሳይሆን፣ የአካባቢውን ማኅበረሰብ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥና የኑሮ ውድነትን ለማቃለል በግብርናው ዘርፍ ላይ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ይገኛል። ከተማ አስተዳደሩ በዘንድሮው የመኸር እርሻ ወቅት አርሶ አደሩን በምርጥ ዘር፣ በማዳበሪያ እንዲሁም በትራክተር እገዛ በወቅቱ ተደራሽ ለማድረግ የተለያዩ ሥራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል።   የከተማ አስተዳደሩ የግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ደጀኔ በቀለ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በአስተዳደሩ የከተማ ግብርና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ያለው ሚና ከፍተኛ ነው። በከተማው በዘንድሮው የምርት ዘመን 95 ሺህ 500 ሄክታር መሬት በማልማት 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰበሰብ የታቀደ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ በአሁኑ ወቅት 89 ሺህ ሄክታር መሬት ታርሶ ለዘር መዘጋጀቱን ተናግረዋል። ከታቀደው መሬትም 80 በመቶው በትራክተር የታረሰ እንደሆነም አክለዋል። እስካሁንም ከ3 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ምርጥ ዘር መሸፈኑን ጠቁመው፣ አሁን ላይ ያለው ዝናብ ለእርሻው አመቺ በመሆኑ እንደ ገብስ፣ ስንዴና ማሽላ ያሉ የሰብል ዓይነቶች እየተዘሩ መሆኑን ተናግረዋል። በግብዓት አቅርቦትም ከታቀደው 162 ሺህ በላይ የአፈር ማዳበሪያ፣ 126 ሺህ መቅረቡንና ከዚህም ውስጥ እስካሁን 62 ሺህ ኩንታል ለአርሶ አደሮቹ መሰራጨቱን አንስተዋል። በተጨማሪም የተፈጥሮ ማዳበሪያ በስፋት ጥቅም ላይ እንደሚውል ጠቁመዋል። ዘርፉን በማጠናከር የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በስፋት ለመጠቀም በተሰጠው ትኩረት ቀደም ሲል በከተማዋ 7 ብቻ የነበሩትን የትራክተሮች ቁጥር በአሁኑ ወቅት ወደ 67 ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል።   እንዲሁም 80 ሺህ ኩንታል የተለያዩ ምርጥ ዘሮች ለአርሶ አደሩ እየቀረበ መሆኑን አክለዋል። በከተማው ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር አርሶ አደሮች የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በሙሉ አቅም እንዲጠቀሙ የግንዛቤ ማሳደጊያ ስልጠና የተሰጠ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅትም ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው ይገኛል ብለዋል።    
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ መነቃቃትና ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ ሚና እያበረከተ ነው 
Jun 20, 2026 743
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 13/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ መነቃቃትና ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ ሚና እያበረከተ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡሉልታ ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ በብዝኃ ኢኮኖሚ መርህ ላይ በመመስረት በግብርና፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም፣ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ እንዲሁም በኢንዱስትሪ ዘርፎች ሰፊ እምርታዊ ለውጥ እያስመዘገበች ትገኛለች። ኢትዮጵያ በኢንዱስትሪው ረገድ ወደ ላቀ ምዕራፍ ላይ እንድትደርስና በዘርፉ የሀገርን ብልፅግና ለማረጋገጥ ታስቦ የተወጠነው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ዘንድሮ ለአራተኛ ጊዜ በስኬት ተካሂዷል። በዚህም የኢትዮጵያን ተወዳዳሪነት የሚያሳዩ አዳዲስ የኢንዱስትሪ ቴክኖሎጂዎችና ሌሎችም ቀርበው በስኬታማነት ተከናውኗል፡፡ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡሉልታ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉን በማነቃቃት ረገድ ባለፉት ዓመታት ተጨባጭ ኢኮኖሚያዊ ስኬቶችን አስመዝግቧል፡፡ ንቅናቄው የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉን በማሳደግና መዋቅራዊ ሽግግርን በማምጣት ለሀገሪቱ ኢንዱስትሪዎች ጠንካራ መሠረት መጣሉንም ተናግረዋል፡፡ በዚህም ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ ለውጥ መጥቷል፤ የገቢ ንግድን በአገር ውስጥ ምርቶች በመተካት የውጭ ምንዛሬን ማዳን መቻሉን እንዲሁም የባለሀብቱን ተሳትፎና የሀገር ውስጥ ኢንቨስትመንትን በማሳደግ ረገድ ትልልቅ ስኬቶች ማስመዝገቡን ተናግረዋል፡፡ መንግሥት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት መዋቅራዊ ሽግግሩ በፈጣን ሁኔታ ለውጥ በማሳየት ላይ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል፡፡ ግንዛቤን በማስጨበጥ፣ ቀጣይነት ያለውና ጥራት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲመጣ በማድረግ እንዲሁም የኢንዱስትሪዎች ተወዳዳሪነት ጎልቶ እንዲታይ በማድረግ ረገድ አበረታች ውጤቶች ተገኝተዋል ብለዋል። የአምራች ኢንዱስትሪው የማምረት አቅምና ምርታማነት በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን ጠቅሰው የኢንዱስትሪው አጠቃላይ የማምረት አቅም አጠቃቀም 66 ነጥብ 3 በመቶ መድረሱን ገልጸዋል። የአምራች ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ፈጣን ዕድገት እያስመዘገበ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በተደረጉት መዋቅራዊ ለውጦች ምክንያት በሁሉም ዘርፍ የተሻሉ ውጤቶች እየታዩ መሆናቸውን ጠቅሰው ዘርፉ ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል ይዞ ከመምጣቱም በላይ ለሀገራዊ ብልጽግና መረጋገጥ ትልቅ አቅም እየሆነ ይገኛል ብለዋል፡፡
በወላይታ ዞን በዘንድሮ መኸር እርሻ ከ132 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይለማል
Jun 20, 2026 392
ወላይታ ሶዶ፤ ሰኔ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወላይታ ዞን በዘንድሮው የመኸር ወቅት ከ132 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች እንደሚለማ የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የወላይታ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ ዘማች ሶርሳ (ዶ/ር)ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው መኸር እርሻ 132 ሺህ 776 ሄክታር መሬት በአዝዕርትና በሆርቲካልቸር ሰብሎች ይለማል። ከሚለማው መሬትም ከ19 ሚሊዮን 96 ሺህ 767 ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ግብ ተቀምጦ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የመኸር ወቅት የግብርና ልማቱን ውጤታማ ለማድረግና ምርታማነትን ለማሳደግም 112 ሺህ 979 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑን ኃላፊው ገልጸዋል። በዞኑ ከሚለማው መሬት አብዛኛው በሜካናይዜሽን የሚታረስና በኩታ ገጠም የሚለማ መሆኑንም ጠቁመዋል። አርሶ አደሮች በጋራ አልምተው ውጤታማ እንዲሆኑ መምሪያው ከግብዓት አቅርቦት ጀምሮ የባለሙያ ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝም አስረድተዋል።   ኢዜአ ያነጋገራቸው የዳሞት ዋጃ ቀበሌ አርሶ አደሮች ፤ በመኸር እርሻ የተሻለ ውጤት ለማግኘት ማሳቸውን እያዘጋጁ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ባለሙያዎችም የሙያ ምክር ከመስጠት ጀምሮ በተለያየ መንገድ እያገዟቸው መሆኑን ተናግረዋል።   የዋጃ ቀሮ ቀበሌ አርሶ አደር ወይዘሮ ቆንጂት ዋትሮ በበኩላቸው፤ ማሳቸውን በተደጋጋሚ በማረስ ለዘር ዝግጁ ማድረጋቸውን ገልጸዋል።
የኢንቨስትመንት ተወዳዳሪነትን ለማረጋገጥ አመራሩ ነባራዊ ሁኔታን በአግባቡ በመረዳት ጥረቱን ማጠናከር አለበት
Jun 20, 2026 416
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 13/2018 (ኢዜአ)፦የተለመደውን አሠራር በመከተል የኢንቨስትመንት ተወዳዳሪነትን ማረጋገጥ ስለማይቻል አመራሩ ነባራዊ ሁኔታውን በአግባቡ በመረዳት ጥረቱን ማጠናከር አለበት ሲሉ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ ተናገሩ። በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ የተመራው ከፍተኛ የፌዴራል እና የክልል አመራሮች ቡድን የገዳ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ጎብኝቷል። በዚሁ ጊዜ ፕሬዚዳንቱ እንዳሉት የተለመደውን አሠራር በመከተል የኢንቨስትመንት ተወዳዳሪነትን ማረጋገጥ ስለማይቻል የለውጥ አመራሩ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ አስቀድሞ በመረዳት ስትራቴጂዎች ቀርጾ መንቀሳቀስ አለበት።   የገዳ ልዩ ኢኮኖሚ ዞንም በዚህ መነሻነት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት የተለያዩ የኢንቨስትመንት ሥራዎች ውስጥ መግባቱን ገልጸዋል። ገዳ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር ዓላማን በማሳካት ወደ አዲስ ምዕራፍ የሚያሸጋግር መሆኑንም ጠቁመዋል። ልዩ የኢኮኖሚ ዞኑ የመሠረተ ልማት ዝግጅት ምዕራፍን በማለፍ ካፒታል፣ ምርታማነትና ከተሜነት የሚገናኙበትና የጋራ ፍሰታቸውን የሚያጠናክሩበት መሆኑንም ተናግረዋል። እስካሁን ባለው እንቅስቃሴ የንግድና ሎጂስቲክስ፣ ግብርና ምርት ማቀነባበር፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ማዕድን፣ አገልግሎትና ሌሎች ዘርፎች በዞኑ ወደ ሥራ ገብተዋልም ነው ያሉት። በእነዚህ ሥራዎች ላይ ኢትዮጵያውያን ባለሀብቶችን ጨምሮ የቻይና፣ የአሜሪካ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ የሆላንድ፣ የጣሊያንና የሌሎች አገራት ኢንቨስተሮች እንደሚገኙም አንስተዋል።   የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግርን የሚያረጋግጡ እነዚህን ስትራቴጂካዊ እርምጃዎች በማጠናከር፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪነትን ይበልጥ የሚያሳድግ ይሆናል ብለዋል። በዚህ ጉብኝት ላይ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማክሮ ኢኮኖሚ አማካሪ አምባሳደር ግርማ ብሩ፣ የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) እና ሌሎች የክልልና የፌዴራል ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
በክልሉ ከተሞችን ዘመናዊና ምቹ የመኖሪያ አካባቢ የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ ቀጥሏል
Jun 20, 2026 359
ቡታጅራ ፤ ሰኔ 13/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከተሞችን ዘመናዊና ምቹ የመኖሪያ አካባቢ የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ገለጸ። የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ ጨምር ኃይሌ፤ በክልሉ በተለያዩ ከተሞች ሁሉን አቀፍ የሆነ የኮሪደር ልማት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የከተሞቹ ልማት የአስፋልት መንገዶችን ጨምሮ፣ የእግረኞች እና የሳይክል መንገድ እንዲሁም ለመዝናኛ ምቹ የሆኑ አረንጓዴ ስፍራዎችን በማካተት ግንባታው እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በዚህ ረገድ ቡታጅራ ከተማ በኮሪደር ልማትም ይሁን በወንዝ ዳር ልማት ፕሮጀክት የምትጠቀስ መሆኗን አንስተው፣ በሌሎች የክልሉ ማዕከል ከተሞችም መቀጠሉን ተናግረዋል። የወንዝ ዳር ልማት ፕሮጀክት ከቡታጅራ በተጨማሪ በወራቤ ከተማም እየተሠራ መሆኑን አንስተው፣ በክልሉ ከተሞችን ዘመናዊና ምቹ የመኖሪያ አካባቢ የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። በሰባት የክልል ማዕከል ከተሞች 165 ኪሎ ሜትር ኮሪደር ልማት በሁለት ምዕራፍ ግንባታቸውን ለማጠናቀቅ በተቀናጀ መልኩ እየተሠራ መሆኑን አንስተው፣ አሁን ላይ 61 ኪሎ ሜትር ተጠናቆ ለአገልግሎት በቅቷል ብለዋል። በክልሉ የገጠር ኮሪደር ልማትን በልዩ ትኩረት በመሥራት የአርሶ አደሮችን አኗኗር ከማሻሻል ባለፈ ከከተሞች ጋር የማስተሳሰር ሥራ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም