ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በሲዳማ ክልል በበልግ ከሚለማው ማሳ 80 ከመቶ በላይ የሚሆነው በዘር ተሸፍኗል 
Apr 25, 2026 64
ሀዋሳ ፤ ሚያዝያ 17/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በበልግ ወቅት ከሚለማው ማሳ ከ80 ከመቶ በላይ የሚሆነው በዘር መሸፈኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በተያዘው የበልግ ወቅት ከ152 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአዝርእት፣ በስራስር አትክልትና በሌሎች ሰብሎች የመሸፈን ስራ እየተከናወነ ነው፡፡ በዚህም እስካሁን ከ80 ከመቶ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን ጠቅሰው በምርት ዘመኑ ከሚለማው ማሳ ከ24 ነጥብ 1 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡ በክልሉ በዋናነት ከሚለማው የአዝርእት ሰብል በቆሎ ቀዳሚ መሆኑን ያነሱት ኃላፊው ፤በበቆሎ ማሳ ውስጥ ቦሎቄን በስብጥር በመዝራት ከተመሳሳይ መሬት የተለያየ ምርት በማግኘት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት የማሳደግ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡   የምግብ ዋስትናን በዘላቂነት የሚያረጋግጡ ድንችና ስኳር ድንችን ጨምሮ ሌሎች የስራስር ምርቶችም ከ50 ሺህ ሄክታር በላይ የማሳ ሽፋን እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡ በልግ አብቃይ በሆኑ የክልሉ አካባቢዎች የተሻለ የዝናብ መጠን፣ ስርጭትና የአርሶ አደር ተሳትፎ መኖሩን የገለጹት ሃላፊው የዘር መዝራት ስራውን በአንድ ሳምንት ውስጥ ለማጠናቀቅ በንቅናቄ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ በምርት ዘመኑ የሚጠበቀውን ምርት ለማግኘት ከማሳ እስከ ግብዓት አቅርቦት በቂ ዝግጅት መደረጉን የጠቀሱት ኃላፊው፤ 90 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያና 17 ሺህ ኩንታል የበቆሎ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ገልጸዋል፡፡ የሃዋሳ ዙሪያ ወረዳ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዲሱ ደሳለኝ በበኩላቸው፤ ወረዳው በልግ አብቃይ ከሆኑ የክልሉ አካባቢዎች ቀዳሚ መሆኑን ጠቅሰው ከ18 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት ሙሉ በሙሉ በዘር ተሸፍኗል ብለዋል፡፡   ከዚህ ውስጥም ከ11 ሺህ 300 በላይ ሄክታር በላይ ማሳ በበቆሎ የተሸፈነ ሲሆን የአረም፣ የተባይና በሽታ ቁጥጥርን ጨምሮ የማሳ እንክብካቤ ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በወረዳው የለቡ ኮረሞ ቀበሌ ሞዴል አርሶ አደር ሳሙኤል ተካራ ፤በበልግ በቆሎ በሚያለሙበት አምስት ሄክታር ማሳ ላይ ቦሎቄን በስብጥር በመዝራት ተጨማሪ ምርት ለማግኘት እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡   ካለፈው ዓመት ጀምሮ በቆሎን በኩታ ገጠም ማምረት መጀመራቸውን ገልጸው ይህም ማሳቸውን ለዘርም ሆነ ለአረም ስራ ምቹ እንዲሆነና ካለሙት የበቆሎ ሰብል እስከ 150 ኩንታል ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል፡፡ ሌላው የቀበሌው አርሶ አደር ናትናኤል ሁሪሶ በበኩላቸው፤ ሁለት ሄክታር ማሳቸውን በበቆሎ ዘር ሸፍነው የአረምና የማሳ እንክብካቤ ስራ እያከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡   ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በወቅቱ ማግኘታቸውን የተናገሩት አርሶ አደሩ የግብርና ባለሙያዎች ድጋፍም እንዳልተለያቸውና ሰብሉ በተገቢው ቁመና ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በክልሉ በመኸር አዝመራ ምርታማነትን የሚያሳድጉ ግብዓቶችንና አዳዲስ አሰራሮችን ለመተግበር ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል
Apr 25, 2026 38
ባህር ዳር፤ ሚያዝያ 17/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በመጪው የመኸር አዝመራ ምርታማነትን የሚያሳድጉ ግብዓቶችንና አዳዲስ አሰራሮችን ለመተግበር ልዩ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የ2018/2019 የመኸር ሰብል ልማት የንቅናቄ መድረክ በባህር ዳር ከተማ እያካሄደ ይገኛል።   የቢሮው ኃላፊ ደረጀ ማንደፍሮ በመድረኩ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው የመኸር ምርት ዘመን ምርታማነትን የሚጨምሩ ቴክኖሎጂዎችን፣ ግብዓቶችንና አዳዲስ አሰራሮችን ለመተግበር ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል። በምርት ዘመኑ ከ5 ነጥብ 5 ሚሊየን ሄክታር በላይ መሬት በማልማት 205 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱን ገልጸዋል። ግብርናውን ከኃላ ቀር የአመራረት ዘይቤ በማላቀቅ ወደ ኢንዱስትሪ መር እና ለውጭ ገበያ የሚተርፍ ምርት የማምረት ሂደት ለማሳደግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። ይህንን ግብ ለማሳካትም የኩታ ገጠም እርሻን ማስፋፋት፣ የግብርና ሜካናይዜሽን አሰራርን መከተልና የአፈር አሲዳማነትን በኖራ የማከም ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑን ኃላፊው ጠቁመዋል።   በክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ምርምር ዳይሬክተር ተስፋዬ ፈይሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ምርታማነትን ለማሳደግ የአፈር ጤንነትን መጠበቅ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ በአሲድ የተጠቃውን መሬት በኖራ ማከም ስራ ይሰራል ያሉት ዳይሬክተሩ፤ ምርምርን መሰረት ባደረገ መልኩ የኖራ፣ የተፈጥሮ ማዳበሪያ እና የቨርሚ ኮምፖስት አጠቃቀምን በማሳደግ ምርታማነትን ለመጨመር እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። በንቅናቄ መድረኩ የክልሉ የግብርና አመራሮች፣ የዘርፉ ባለሙያዎችና የአጋር አካላት ተወካዮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
በዞኑ የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል 70 ሚሊዮን የተሻሻለ የቡና ችግኝ ለተከላ ተዘጋጅቷል
Apr 25, 2026 53
አዶላ፤ ሚያዝያ 17/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን የበልግ ዝናብ ወቅትን በመጠቀም የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል 70 ሚሊዮን የተሻሻለ የቡና ችግኝ ለተከላ መዘጋጀቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በጽህፈት ቤቱ የቡናና ሻይ ልማት ባለሙያ አቶ ብርሀኑ ፈይሳ እንደገለጹት፤ ዘንድሮ የተዘጋጀው የቡና ችግኝ ከቀደሙት ዓመታት ብልጫ እንዳለው ጠቅሰው፤ በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የበልጉን ዝናብ በመጠቀም እስካሁን በ9 ሺህ 300 ሄክታር መሬት ላይ ተከላ የመከናወኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ከ40 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን ተናግረዋል።   እየተተከሉ ያሉ ችግኞች አብዛኞቹ ከግብርና ምርምር ማዕከላት የተገኙና ከአካባቢ ዘር የተዘጋጁ መሆናቸውንም ባለሙያው ገልጸዋል። የችግኝ ዝርያዎቹ በተለይም ከጅማ ግብርና ምርምር ማዕከል፣ ከይርጋለም እና ከአወዳይ ግብርና ምርምር ጣቢያዎች የተለቀቁ መሆናቸውንም ነው የገለጹት። እየተተከሉ ያሉ ዝርያቸው የተሻሻለ የቡና አይነቶች በሄክታር ከ12 እስከ 15 ኩንታል ምርት መስጠት የሚችሉ መሆኑን ገልጸው፤ በነባሩ ዝርያ የሚገኘው ምርት ከ6 ኩንታል ያነሰ እንደነበር አስታውሰዋል። የተተከለው ችግኝ ከአምስት ዓመት ባነሰ ጊዜ ውስጥ ምርት መስጠት የሚጀምር ሲሆን፣ ነባሩ ዝርያ ምርት ለመስጠት ከ7 እስከ 8 ዓመት ይፈጅበታል ብለዋል። በዞኑ ውስጥ ለቡና ልማት ተስማሚ የሆነ ከ10 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት መዘጋጀቱንና የዞኑ አርሶ አደሮችም ከሰብልና ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን በቡና ልማት ላይ እየተሳተፉ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። በዞኑ በ12 ወረዳዎችና በ157 ቀበሌዎች ከ177 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቡና ልማት የተሸፈነ መሆኑንም አመልክተዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በአፕል ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጠቃሚነታቸው እያደገ ነው
Apr 25, 2026 55
አምቦ፤ ሚያዝያ 17/2018 (ኢዜአ)፦በምዕራብ ሸዋ ዞን በአፕል ልማት ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች ከምርቱ በሚያገኙት ገቢ ተጠቃሚነታቸው ማደጉን ገለጹ። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት በበኩሉ በዞኑ ለፍራፍሬ ልማት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ በተሰራው ስራ ውጤት እየተገኘ መሆኑን አረጋግጧል። ቀደም ሲል በዞኑ የፍራፍሬ ልማት ያልተለመደ ቢሆንም፣ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በተደረገ የተቀናጀ ጥረት አርሶ አደሩ ከጥራጥሬ ሰብሎች በተጨማሪ በፍራፍሬ ልማት በመሰማራት ገቢውን እያሳደገ ይገኛል።   በዞኑ የጅባትና የሚዳቀኝ ወረዳ አርሶ አደሮች ከግብርና ባለሙያዎች ያገኙትን የሙያና የችግኝ ድጋፍ ተጠቅመው ወደ ስራ መግባታቸውንና ውጤታማ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የጅባት ወረዳ አርሶ አደር ሀይሉ ኢትቻ "በአፕል ልማት በመሳተፍ ምርቱን ለገበያ በማቅረብ የተሻለ ገቢ እያገኘሁ ነው'' ብለዋል። ልማቱን ቀደም ብለው በመጀመራቸው የአፕል ምርት ልምዳቸውን ለአካባቢው አርሶ አደሮች እያካፈሉ መሆኑንም ተናግረዋል።   ሌላው የሚዳቀኝ ወረዳ አርሶ አደር ደረጄ አብሼ፤ በባለሙያዎች የተሰጣቸውን ግንዛቤና ክትትል ተጠቅመው የአፕል ተክሉን በመንከባከባቸው ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ተናግረዋል። ከአፕል ልማት በሚያገኙት ተጨማሪ ገቢ ልጆቻቸውን በተሻለ ሁኔታ እያስተማሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ባለሙያ የሆኑት አቶ መንገዱ ጉርሙ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት በዞኑ ጅባት፣ ሚዳቀኝ፣ ኢልፋታ፣ አምቦ እና ወልመራ አፕል በስፋት የሚመረትባቸው ወረዳዎች ሲሆኑ፣ በሌሎች ወረዳዎችም እንደየአየር ንብረታቸው ልማቱን የማስፋፋት ስራ እየተከናወነ ይገኛል።   በአሁኑ ወቅት በዞኑ በ3 ሺህ 110 ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ ፍራፍሬዎች እየለሙ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 265 ሄክታሩ በአፕል የተሸፈነ ነው ብለዋል። በአፕል እየለማ ከሚገኘው መሬትም እስካሁን ባለው ሂደት 11 ሺህ 720 ኩንታል መሰብሰብ ተችሏል ነው ያሉት። አርሶ አደሩን ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ከወረዳ ግብርና መዋቅሮችና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የተሻሻሉ ዝርያዎችን በማቅረብና ስልጠናዎችን በመስጠት ላይ መሆኑንም ተናግረዋል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን የ2018/19 የምርት ዘመን ምርታማነትን ለማሳደግ ለአርሶአደሮች ግብዓት እየቀረበ ነው 
Apr 25, 2026 79
ነቀምቴ ፤ ሚያዝያ 17/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ወለጋ ዞን የ2018/19 የምርት ዘመን ምርታማነትን ለማሳደግ የግብዓት አቅርቦት ላይ ትኩረት መደረጉን የዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት አስታወቀ። በዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት የግብዓት አቅርቦት እና ፍላጎት ቡድን መሪ አቶ ለሚ አጋ፤ የአርሶ አደሩን የግብዓት ፍላጎት በመለየት መጪውን የምርት ዘመን ውጤታማ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   በዚህም 463 ሺህ 744 ኩንታል ማዳበሪያ ወደ ዞኑ መግባቱን ገልጸው 311 ሺህ 877 ኩንታሉ ለአርሶ አደሩ ለማሰራጨት ተችሏል ነው ያሉት። እንዲሁም ከምርጥ ዘር ጋር በተያያዘም ከ13 ሺህ ኩንታል በላይ የቀረበ ሲሆን ከ10 ሺህ ኩንታል በላይ የሚሆነው ለአርሶ አደሩ መቅረቡን ገልጸዋል። በዘንድሮው የምርት ዘመን ከ203 ሺህ 825 አርሶ አደሮች በላይ የሚሳተፉ ሲሆን ከ800 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይለማል ተብሎ እንደሚጠበቅ አቶ ለሚ ተናግረዋል። በዞኑ በቆሎ፣ ማሽላ፣ ጤፍ፣ ሱፍ እና ሰሊጥ በስፋት የሚመረት መሆኑን ጠቁመው የምርት ማሳደጊያ ግብዓቶቹን ለአርሶ አደሩ በፍትሃዊነት ተደራሽ በማድረግ ላላስፈላጊ ወጪ እንዳይዳረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። የዞኑ አርሶ አደሮችም መንግስት ከወዲሁ ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ሰጥቶ በመስራት ያደረገው ቅድመ ዝግጅት እንዳስደሰታቸው ገልጸዋል።   በዞኑ ኡኬ ከተማ ነዋሪና አርሶ አደር አቶ ጫሊ ከበደ ፤ባላቸው 30 ሄክታር መሬት ላይ በእርሻ ኢንቨስትመንት መሰማራታቸውን ገልጸው ለስራው አስፈላጊ የሆነውን ግብዓት እያገኙ መሆናቸውን አስረድተዋል። በወረዳው ያለውን ምቹ የአየር ንብረት እና ለም መሬት በመጠቀም በስፋት በቆሎ በማምረት ላይ እንደሚገኙም ገልጸዋል።   አርሶ አደር አቶ ተመስገን ሁንደራ፤ ባላቸው ዘጠኝ ሄክታር መሬት ላይ በቆሎ በማምረት ላይ እንደሚገኙ ተናግረው የምርት ማሳደጊያ እያስገቡ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በክልሉ በከተማና ገጠር ወረዳዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት እያጎለበቱ የሚገኙ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Apr 24, 2026 305
ሐረር፤ ሚያዝያ 16/2018(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በከተማና ገጠር ወረዳዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት እያጎለበቱ የሚገኙ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በትኩረት እንደሚሰራ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ አስታወቁ። የሐረሪ ክልል መንግስት አስፈጻሚ አካል የበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ ተጠናቅቋል። በግምገማ መድረኩም የአስፈጻሚው አካላት የበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት የስራ አፈጻጸም ሪፖርት ቀርቦ ሰፊ ውይይት ተካሄዷል።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በመድረኩ ማጠቃለያ እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል። በተለይ በክልሉ ከተማና ገጠር ወረዳዎች ለህዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡና ተጠቃሚነትን ያሳደጉ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተዋል። እንዲሁም በአመራሩ በኩል በክልሉ ለሚከናወኑ ቀጣይ ተግባራት ተነሳሽነትን ያጎለበቱ መሆናቸውን ጠቁመው ተግባራቱ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አመላክተዋል። የተከናወኑት ተግባራት አበረታች ቢሆንም የአፈጻጸም ክፍተት የታየባቸው አንድ አንድ ተግባራትን በቀጣይ ሶስት ወራት በአግባቡ መፈጸም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።   በተሻለ ፍጥነትና ጥራት እንዲሁም በተቀናጀ መልኩ ስራዎችን በማከናወን የህዝቡን እርካታ ማጎልበት እንደሚገባ አሳስበዋል። እንዲሁም የአፈጻጸም ቁርጠኝነትን በማጎልበት፣ ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከርና የጋራ ግብን በመሰነቅ የተጀመሩ የልማት፣ የሰላም፣ የመልካም አስተዳደርና ሌሎች ተግባራትን በበለጠ ስኬታማ ማድረግ ይገባል ብለዋል።
ሀገራዊ ዕቅዶችን በላቀ ውጤት ለመፈጸም ሁሉም አመራር በቀሪ ወራት በፍጥነትና በትኩረት መትጋት ይጠበቅበታል
Apr 24, 2026 448
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018(ኢዜአ)፦ በቀሪ ወራት ሀገራዊ ዕቅዶችን በላቀ ውጤት ለመፈጸም ሁሉም አመራር በፍጥነትና በትኩረት መትጋት እንደሚጠበቅበት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ አሳሰቡ። የ2018 በጀት ዓመት የሦስተኛው 100 ቀን የሥራ አፈጻጸም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ እና የፌዴራል ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተገምግሟል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በዚህ ወቅት መንግሥት በወሰዳቸው የጠራ የፖሊሲ እርምጃዎች በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በዲፕሎማሲና በሌሎች መስኮች ትላልቅ ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል።   ​በኢኮኖሚው ረገድ በሁሉም ዘርፎች እመርታ መምጣቱን ጠቅሰው፥ የአረንጓዴ ዐሻራ፣ የስንዴ ልማት፣ የሌማት ትሩፋት መርኃ ግብሮች የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ ሚና እየተጫወቱ ነው ብለዋል። የገበታ ፕሮጀክቶችና የኮሪደር ልማት ለሀገር ገፅታ መለወጥ፣ ለቱሪዝም ማደግና ለከተሞች ምቹነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን አንስተዋል። በዲጂታል ዘርፍና በመሶብ የአንድ ማዕከል የመንግሥትን አገልግሎቶች በማዘመን በኩል ለውጥ ማምጣቱን ገልጸዋል። ባለፉት ስምንት ዓመታት ኢትዮጵያ የተደቀኑባትን ትላልቅ ፈተናዎችና የተከማቹ ዕዳዎችን በመሻገር የከፍታ ምዕራፍ ላይ መድረሷንም ተናግረዋል። ከለውጡ በፊት በሕዝቡ ዘንድ የአፈጻጸም ድክመት ማሳያ የሆኑ የመንግሥት የልማት ፕሮጀክቶች፥ የጥራት ጉድለት፣ የበጀት ብክነት፣ የጊዜ መዘግየት ምሳሌዎች ሆነው መቆየታቸውን አውስተዋል። ሀገራዊ ለውጡ ይህን ግዙፍ ችግር ማስወገዱን በማንሳት፥ አሁን ላይ ማንኛውም ፕሮጀክት ሳይገመገምና ሳይጠናቀቅ ወደ አዲስ ሥራ የማይገባበት ጥብቅ ሥርዓት መዘርጋቱን አረጋግጠዋል። የመደመር መንግሥት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነትና በጥራት በመፈጸም የሚታወቅ ሆኗልም ነው ያሉት። የመካከለኛ እና የአጭር ጊዜ የልማት ዕቅዶች እንዲሁም የሪፎርም ሥራዎች በጥብቅ ዲሲፕሊን እንዲመሩ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው፥ ለዚህም የአንድ ዕቅድ አንድ ሪፖርት ሥርዓት መዘርጋቱን ገልጸዋል።   በመድረኩ የሦስተኛውን የ100 ቀናት አፈጻጸም ሪፖርት ያቀረቡት የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ በረከት ፍስሐፅዮን በበኩላቸው፥ ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ሀገራዊ ኢኒሼቲቮችንና ፕሮጀክቶችን በዕቅድ የመፈጸምና የመከታተል ባህል ዳብሯል ብለዋል። በተለይም የአንድ ዕቅድ አንድ ሪፖርት ሥርዓት መኖሩ መንግሥት ለሕዝብ የገባውን ቃል መተግበሩን በመከታተል የላቀ አፈጻጸም ለማስመዝገብ ትልቅ ለውጥ አምጥቷል ነው ያሉት። በመድረኩ የተሳተፉ አመራሮች በሰጡት አስተያየት፥ ባለፉት ዓመታት ፈጠራን መሠረት ያደረገና ፈተናዎችን የተሻገረ የተቀናጀ አሠራርን በመከተል በሁሉም መስክ ስኬት መመዝገቡን ገልጸዋል። በብዝሃ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ በዲጂታል፣ በሰብዓዊ ድጋፍና የምግብ ሉዓላዊነት የመጡ ለውጦች ለፈተናዎች የማትበገር ሀገር ለመገንባት ጠንካራ መሠረት ሆነዋል ነው ያሉት።   ​ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በሰጡት ማጠቃለያ እስካሁን የተመዘገቡ ስኬቶችን በላቀ ውጤት ማስቀጠል መትጋት ወሳኝ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል። በተለይም መንግሥት በአምሥት ዓመታት ሊፈጽማቸው ለሕዝብ ቃል የገባቸውን ተልዕኮዎች ማሳካት ከሁሉም አመራር እንደሚጠበቅ አስገንዝበዋል። ለዚህም በሁሉም ዘርፎች በፍጥነት፣ በትኩረትና በትጋት ለላቀ ድል መሥራት ወሳኝ መሆኑን አሳስበዋል።
በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ302 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ቀርቧል  
Apr 24, 2026 117
ቦንጋ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ302 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ መቅረቡን የክልሉ ማዕድንና ኢነርጂ ልማት ኤጀንሲ አስታወቀ። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የክልሉ ማዕድንና ኢነርጂ ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ወልያብ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ በክልሉ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለወርቅና ለድንጋይ ከሰል ልማት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።   በበጀት ዓመቱም ከክልሉ 350 ኪሎ ግራም ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ለማቅረብ ታቅዶ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ302 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ መቅረቡን ገልጸዋል። የወርቅ ምርቱን 338 ማህበራት እና ግለሰቦች በዘመናዊና ባህላዊ መንገድ እንዳመረቱት ገልጸዋል፡፡ እንደ ዋና ዳይሬክተሩ ገለጻ፣ በዘጠኝ ወር ውስጥ በወርቅ ምርት ለሚሰማሩ 202 አዲዲስ ማህበራትም ፍቃድ ተሰጥቷል። የተጠናከረ የድጋፍና ክትትል ሥራ መከናወኑ፣ የወርቅ ምርት ያለባቸው አዳዲስ አካባቢዎች ወደሥራ መግባት እና በዘርፉ ህገ-ወጥነትን ለመከላከል የተሰሩ ስራዎች ለወርቅ ምርቱ መሻሻል ምክንያት መሆናቸውን አንስተዋል። የግብይት ማዕከላት መጠናከርና አቅም ያላቸው ባለሀብቶች በዘርፉ መሰማራታቸው ትልቅ አስተዋፅኦ ማድረጉንም የኤጀንሲው ዳይሬክተር ጌታቸው (ዶ/ር) ጠቁመዋል። የድንጋይ ከሰል በክልሉ በሰፊው የሚመረት ሌላው ማዕድን መሆኑን ጠቁመው፣ በዘጠኝ ወሩ 150 ሺህ ቶን ለማምረት ታቅዶ እስካሁን ከ122 ሺህ ቶን በላይ ማምረት ተችሏል ብለዋል። በቀጣይም በክልሉ የማዕድን ሀብት ላይ ጥናት በማድረግ ልማቱን በስፋት አጠናክሮ ለማስቀጠልም እንቅስቃሴ መጀመሩን ገልፀዋል።
ለመጪው የመኸር ወቅት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ርብርብ ይደረጋል
Apr 24, 2026 149
ደብረ ብርሃን፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በሰሜን ሸዋ ዞን ለመጪው የመኸር ወቅት ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ለተያዘው ግብ ስኬት ርብርብ የሚደረግበት መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። መምሪያው ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ የ2018/19 የመኸር ሰብል ልማት የእቅድ ትውውቅ የንቅናቄ መድረክ በደብረ ብርሃን ከተማ ዛሬ አካሄዷል።   የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ታደሰ ማሙሻ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ በግብርናው ዘርፍ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለወጪ ንግድ የሚተርፍ ምርት ለማምረት እየተሰራ ነው። በዞኑ መጪው የመኸር ወቅት እርሻ ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። አርሶ አደሩ የምርት ማሳደጊያ ቴክኖሎጂዎችን፣ አዳዲስ አሰራሮችንና ግብዓትን በመጠቀም የተያዘውን ግብ እንዲያሳካ በየደረጃው ያለው አመራርና ባለሙያ ጠንክሮ የሚሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   በዚህም በመጪው የመኸር ወቅት 556 ሺህ ሄክታር መሬትን በዘር በመሸፈን 20 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማምረት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅት 90 በመቶ የሚሆነውን መሬት እስከ ሶስት ጊዜ ደጋግሞ በማረስ ለዘር ዝግጁ ማድረግ መቻሉን ጠቁመው ከዚህ ውስጥ 52 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በሜካናይዜሽን የሚለማ ነው ብለዋል። ምርታማነትን ለማሳደግም እስካሁን 650 ኩንታል ማዳበሪያ ወደ ዞኑ በማስገባት ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ይህም አርሶ አደሩ የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባሻገር ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት የሚያስችል ሲሆን የዛሬው መድረክም የተጀመሩ ተግባራትን አጠናክሮ በማስቀጠል ግቡን ለማሳካት ያለመ መሆኑን ጠቁመዋል።   በዞኑ የሲያደብርና ዋዩ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ አንዷለም የሻው እንዳሉት፤ የሞዴል አርሶ አደሮችን ተሞክሮ ወደ ሁሉም አርሶ አደሮች በማሸጋገር ግቡን ለማሳካት ይሰራል። በምንጃር ሸንኮራ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ በቀለ ወንድወሰን በበኩላቸው፤ በሙያቸው አርሶ አደሩን በመደገፍ የሚጠበቅበትን ምርት እንዲያመርት እንደሚያደርጉም ገልጸዋል።   በመድረኩ ላይ በዞኑ ስር የሚገኙ የግብርና አመራሮች፣ ባለሙያዎች፣ ከምርምር ተቋማትና ከደብረ ብርሃን ዩኒቨርሲቲ የመጡ ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያ እያካሄደችው ያለው ሪፎርም ለኢንቨስትመንት ምቹ ምህዳር እየፈጠረ ነው
Apr 24, 2026 81
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ እያከናወነችው ያለው የኢኮኖሚ ሪፎርም፣ምቹና ተገማች የኢንቨስትመንት ምህዳር እየፈጠረ እንደሚገኝ የተባበሩት መንግሥታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት (ዩኒዶ) የዘላቂ ኢንቨስትመንትና ማኅበራዊ ኃላፊነት ዘርፍ ኃላፊ ስቴፋን ክራትዝሽ ገለጹ። ስቴፋን ክራትዝሽ ማሻሻያዎቹ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትንና የአገር ውስጥ ካፒታልን ለመሳብ ፋይዳቸው የጎላ መሆኑን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። ይህም ኢንቨስትመንቱ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለእሴት ሰንሰለት ልማትና ለወጪ ንግድ ዕድገት አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ያስችላል ብለዋል። የኢትዮጵያ ሰፊ የሕዝብ ቁጥር ትልቅ የገበያ ዕድል እንደሚፈጥርና ይህም ባለሀብቶች ሥራቸውን በሀገር ውስጥ እንዲያስፋፉ እንዲሁም እንደ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ባሉ ማዕቀፎች አማካኝነት ወደ ቀጣናዊና አህጉራዊ ገበያዎች እንዲገቡ ዕድል እንደሚሰጥ አመልክተዋል። የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን ከሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪ ልማት ጋር ማመጣጠን አስፈላጊ መሆኑን ያመለከቱት ኃላፊው፣ የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ እንደ የጋራ ሽርክና እና የመንግሥትና የግሉ ዘርፍ አጋርነቶች አስፈላጊ መሆናቸውን አጽንኦት ሰጥተዋል። ጠንካራ የአስተዳደር ሥርዓት ያላቸውና በተለይም የሴቶችንና የወጣቶችን የሥራ ዕድል እንዲሁም የውሳኔ ሰጪነት ሚና የሚያረጋግጡ አካታች ኢንቨስትመንቶች ቅድሚያ ሊሰጣቸው እንደሚገባም ነው ያሳሰቡት። የኢትዮጵያ መንግሥት ከባለሀብቶች ጋር ያለውን ግልጽነትና ትብብር ያደነቁት ኃላፊው፤ የባለሀብቶችን እምነት ለማጠናከርና የንግድ ምህዳሩን ይበልጥ ለማሻሻል በመንግሥትና በግል ዘርፍ መካከል የሚደረገው ውይይት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአህጉሪቱ የኢንዱስትሪ እንቅስቃሴ ውስጥ ግንባር ቀደም ተዋናይ የመሆን ዕድሏ ሰፊ መሆኑንና ለሌሎች የአፍሪካ አገራትም በአርአያነት ልትጠቀስ እንደምትችል አመልክተዋል። ዩኒዶ የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ልማት በቴክኒክ፣ በአቅም ግንባታና በፖሊሲ ማማከር እየደገፈ ይገኛል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በ2018 የበልግ ወቅት እስካሁን ከ840 ሺህ ሔክታር በላይ ማሳ ለምቷል  
Apr 24, 2026 74
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በዘንድሮው የበልግ ወቅት ከ840 ሺህ ሔክታር የሚልቅ ማሳ በዘር መሸፈኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በ2018 የበልግ ወቅት ከ980 ሺህ ሔክታር የሚልቅ ማሳ በማልማት ከ97 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን የቢሮው ምክትልና የእርሻ ዘርፍ ኃላፊ አድማሱ አወቀ ተናግረዋል።   እስካሁንም ለማልማት ከታቀደው ከ840 ሺህ ሔክታር የሚልቀው ማሳ በዘር መሸፈኑን ጠቁመዋል። ለበልፉ ወቅት ሥራ ከ59 ሺህ በላይ ኩንታል የበቆሎ ምርጥ ዘር እና ከ200 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሮች መድረሱንም አረጋግጠዋል። የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ለተጀመረው ጥረት የባለሙያ ድጋፍ መጠናከሩንም አመላክተዋል። በወላይታ ዞን ኪንዶ ኮይሻ ወረዳ የፋጄና ማታ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ጀማነህ ጃምቦ፤ ማሳቸውን በትራክተር አርሰው በበቆሎ እና ካሳቫ ዘር መሸፈናቸውን ገልጸዋል። ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በወቅቱ በመቅረቡ ሥራቸውን በግብርና ባለሙያዎች ታግዘው እየሠሩ መሆናቸውንም አንስተዋል።   በሁምቦ ወረዳ የኮይሻ ኦጎዳማ ቀበሌ አርሶ አደር ደሞዜ ለማ በበኩላቸው፤ በቆሎ እና አደንጓሬ መዝራታቸውን ተናግረው ለሰብላቸው እንክብካቤ በማድረግ የተሻለ ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውን ገልጸዋል። ግብዓቶችን በወቅቱ እንዳገኙ ተናግረው፤ በግብርና ባለሙያዎች አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆናቸውንም አክለዋል።
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተኪ ምርት የማምረት አቅማችንን እንድናጎለብት አግዞናል-አምራቾች
Apr 24, 2026 87
አርባ ምንጭ ፤ሚያዝያ 16/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተኪ ምርት የማምረት አቅማችንን እንድናጎለብት አግዞናል ሲሉ አምራች እንዱስትሪዎች ገለጹ፡፡ "ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት ለኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ" በሚል መሪ ሃሳብ በአርባ ምንጭ ከተማ በተዘጋጀው ክልል አቀፍ ኤግዚቢሽንና ባዛር ላይ የተሳተፉ ኢንዱስትሪዎች በተኪ ምርቶች ያለንን ሚና እንድናጎለብት አስችሎናል ብለዋል።   በክልሉ ጂንካ ከተማ የባስልኤል ኢንጂነርንግ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ አቶ ጌታቸው መሃመድ እንዳሉት፤ ችግር ፈቺ የፈጠራ ስራዎችንና ተኪ ምርቶችን በማምረት ማህበረሰቡን ተጠቃሚ እያደረግን እንገኛለን። በዚህም የውሃ ጉድጓድ መቆፈሪያን ጨምሮ የቡና መቁያና መፍጫ እንዲሁም የገብስ መፈተጊያ ማሽኖችን እያመረትን ነው ብለዋል። በተለይ በውሃ ጉድጓድ መቆፈሪያ ማሽን በከተማው ከ100 በላይ የውሃ ጉድጓዶችን በመቆፈር ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረጋቸውን ነው የተናገሩት። ድርጅታቸው የትራክተር መለዋወጫ ዕቃዎች ማለትም ማረሻዎች፣ መከስከሻዎችና ሌሎች ከውጭ ገብተው ከሚሸጡበት ከ100 እስከ 300 ሺህ ብር ቅናሽ በማድረግ የዶላር ምንዛሬ ጫናን መቅረፍ ችለናል ብለዋል። የሴቶችን ጊዜና ጉልበት የሚቆጥቡና የስራ ጫና የሚቀንሱ የዳጣ ማላሚያ፣ የአተር መከኪያ፣ የሽንኩርት መፍጫና ሌሎቹ ተኪ ምርቶችን ስለማምረታቸው አብራርተዋል፡፡ ለዚህም በመንግስት እና በከተማ አስተዳደሩ እየተደረገላቸው ያለው ድጋፍ እገዛ ማድረጉን አመልክተዋል፡፡   የአካባቢውን የባህል ሽመና የሀገር በቀል ዕውቀት እሴትን በመጨመር አምርቶ ለሀገር ውስጥና ለዓለም አቀፍ ገበያ እያቀረበ መሆኑን የገለጸው ደግሞ በአርባ ምንጭ የጃኖ ዕደ ጥበብ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ፍሬው ቆንጆ ነው። ኢንተርፕራይዙ በዋናነት የእጅ ሽመና በመጠቀም ለፋሽንና ለቤት ቁሳቁስ የሚሆኑ የተለያዩ አልባሳትን በማምረት በተኪ ምርት ጉልህ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተወዳዳሪ የሆኑ ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሬን እንድናድን ብሎም ምርቶቻችን እንድናስተዋውቅ ትልቅ እገዛን አድርጎልናል ብሏል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሰናይት ሰለሞን፥የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም እንዲጎለብት አድርጓል ብለዋል። ንቅናቄው የኢትዮጵያ ምርቶችን ከማስተዋወቅና ተጨማሪ የገበያ ዕድሎችን ከማስፋት ባሻገር የሀገር ውስጥ ምርት አጠቃቀም ላይ ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል ነው ያሉት። በአርባ ምንጭ ከተማ በተዘጋጀው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤግዚቢሽንና ባዛር ከ70 በላይ አምራች ኢንዱስትሪዎች በመሳተፍ ምርቶቻቸውን እያስተዋወቁ ይገኛሉ። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የኢትዮጵያ ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳር የቼክ ሪፐብሊክ ባለሃብቶችን ቀልብ እየሳቡ ነው
Apr 24, 2026 187
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳር የቼክ ሪፐብሊክ አልሚ ባለሃብቶችን ቀልብ እየሳቡ እንደሚገኝ የቼክ ሪፐብሊክ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ራዴክ ሩበሽ ገለጹ። የኢትዮጵያ እና ቼክ ሪፐብሊክ ታሪካዊ ግንኙነትም በሁሉም መስክ የትብብር አድማሱን እያሰፋ እንደሚገኝም ተናግረዋል። የኢትዮ-ቼክ ሪፐብሊክ የፖለቲካል ዲፕሎማቲክ ግንኙነት እ.አ.አ ከ1918 ጀምሮ በታሪካዊ ወዳጅነትና ትብብር እየጎለበተ መምጣቱን መረጃዎች ያመለክታሉ። የቼክ ሪፐብሊክ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚንስትር ራዴክ ሩበሽ ለኢዜአ እንዳሉትም፤ የኢትዮ-ቸክ ሪፐብሊክ ታሪካዊ ግንኙነት በበርካታ ዘርፎች ዕድገት እያስመዘገበ መጥቷል። ለአብነትም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የቼክ አቻቸው ፔትር ፊያላ ይፋዊ የእርስ በዕርስ የሥራ ጉብኝትም የሀገራቱን ታሪካዊ ወዳጅነት የበለጠ በማደስ ጠንካራ መሰረት መጣሉን አስታውሰዋል። በቼክ ሪፐብሊክ ፕራግ ከተማ እ.አ.አ በ2023 የተካሄደው ታላቅ የኢትዮጵያ የጥበብና ባህል አውደ-ርዕይም የሀገራቱን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበተርከቱን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አስቻይ የንግድና ኢንቨስትመንት ምኅዳርም የቼክ ሪፐብሊክ አልሚ ባለሃብቶችን ቀልብ እየሳበ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በተለይም በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የተወሰዱ እርምጃዎች የቼክ ባለሃብትች የኢትዮጵያን የንግድና ኢንቨስትመንት አማራጮች የሚያጤኑበት ዕድል መፍጠሩን አስረድተዋል። ይህም የቼክ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት አማራጭቾ በስፋት ለመሰማራት ከፍተኛ ፍላጎት ማሳደሩን አንስተዋል። የኢትዮ-ቼክ የኢኮኖሚ ስምምነቶችን በሚገባ በመተግበር የሀገራቱን የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር ለማበረታታት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል። ለዚህም የሀገራቱን የንግድና ኢንቨስትመንት ማህበረሰብ የሚያገናኝ የጋራ የኢኮኖሚ ኮሚሽን ለማቋቋም እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የጋራ የኢኮኖሚ ኮሚሽኑም በሀገራቱ መካከል የእርስ በዕርስ የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስርን ለሚፈልጉ ኩባንያዎች ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የንግድና ኢንቨስትመንት ዕድሎች በመዳሰስ የቼክ ባለሃብቶች ሊሰማሩባቸው የሚችሉ መስኮች ተለይተው እየተሰራባቸው መሆኑንም አረጋግጠዋል። በተጨማሪም በቱሪዝም፣ መስኖ፣ ቆሻሻ አወጋገድ፣ በውሃና ንፅህና አጠባበቅ መሠረተ ልማት ዘርፎች በትብብር ለመስራት ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
አዲስ አበባን የሳይንስና የፈጠራ ማዕከል ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ነው-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 24, 2026 162
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- አዲስ አበባን የሳይንስና የፈጠራ ማዕከል የሚያደርጉ ሰፋፊ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ከንቲባ አዳነች ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ 11ኛውን ከተማ አቀፍ የሳይንስ ፈጠራ ስራ አውደ ርዕይ በይፋ ከፍተዋል።   “በሳይንስና ፈጠራ የተካነ ትውልድ ለተምሳሌታዊ ሀገር” በሚል መሪ ሀሳብ የሚደረገው አውደ ርዕይ ዛሬ እና ነገ ክፍት ሆኖ ይቆያል። ከንቲባዋ አውደ ርዕዩን በከፈቱበት ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፣ መድረኩ የከተማዋን የፈጠራ ጉዞ አንድ ደረጃ የሚያራምድ መሆኑን ገልጸዋል። የዛሬው የሳይንስ ፈጠራ ስራ አውደ ርዕይ ዋነኛ ዓላማ ተማሪዎች በክፍል ውስጥ በንድፈ ሀሳብ የተማሩትን ትምህርት በተግባር የሚያሳዩበት መድረክ መፍጠር እንደሆነ አመልክተዋል። አያይዘውም ተማሪዎች የውስጥ ተሰጥዖዋቸውን የሚገልጹበት፣ ለሰሯቸው የፈጠራ ስራዎች ዕውቅናና ማበረታቻ የሚያገኙበት እንዲሁም እርስ በእርስ በትብብር የመስራት ልምድ የሚለዋወጡበት ትልቅ መድረክ ነው ብለዋል።   እውነተኛ እውቀት ችግሮችን ደጋግሞ ማውራት ሳይሆን ለችግሮች መፍትሄ ማፍለቅና ችግርን ወደ ድል መቀየር መሆኑን የጠቀሱት ከንቲባ አዳነች፣ አዲስ አበባን የሳይንስና የፈጠራ ማዕከል ለማድረግ ሰፋፊ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቁመዋል። አሁን ላይ የተጀመሩ ስራዎች ውጤት በተጨባጭ መታየት የጀመረበት ወቅት ላይ መደረሱን ገልጸው፣ ይህ ውጤታማ ጅምር ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሁሉም ባለድርሻ አካላት ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። ዛሬ የፈጠራ ስራቸውን ያቀረቡ ተማሪዎችና መምህራን ላይ ትልቅ ተስፋ እንዳላቸው የገለጹት ከንቲባዋ፣ እነዚህ የፈጠራ ስራዎች አድገውና በልጽገው ለከተማዋ፣ለሀገር ብሎም ለዓለም የሚተርፍ በረከት እንደሚሆኑ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በሳይንስና ፈጠራ የተካነ ትውልድ የሀገርን ብልጽግና ለማረጋገጥ ወሳኝ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 24, 2026 117
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በሳይንስና ፈጠራ የበለፀገ ትውልድ መገንባት ለሀገር ብልጽግና እና ሁለንተናዊ እድገት መሰረት በመሆኑ የከተማ አስተዳደሩ ለዘርፉ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ “በሳይንስና ፈጠራ የተካነ ትውልድ ለተምሳሌታዊ ሀገር” በሚል መሪ ሐሳብ ያዘጋጀው 11ኛው የሳይንስና የፈጠራ ሥራ ዐውደ-ርዕይ በአራዳ ፓርክ እየተካሄደ ይገኛል። በዚህ መድረክ ላይ በርካታ ተማሪዎችና መምህራን የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ለዕይታ አቅርበዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ዐውደ-ርዕዩን በጎበኙበት ወቅት እንደተናገሩት፤ መድረኩ ተማሪዎችና መምህራን የፈጠራ ሥራዎቻቸውን የሚያስተዋውቁበትና እርስበርስ የፈጠራ ሐሳባቸውን የሚለዋወጡበት ወሳኝ ድልድይ ነው። በዐውደ-ርዕዩ የቀረቡት የፈጠራ ውጤቶች ከተማዋን ወደ ስማርት ሲቲ ለመቀየር እየተደረገ ላለው ጥረት ትልቅ ተስፋ የሚሰጥና የምሥራች መሆናቸውንም ገልጸዋል። ማንኛውም የፈጠራ ሥራ ውጤት በትንሽ ጅማሮ የሚነሳ መሆኑን ጠቅሰው፤ መንግሥት እነዚህን የፈጠራ ሥራዎች በፋይናንስና በሙያ በመደገፍ ወደ ላቀ ደረጃ እንዲሸጋገሩ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። በአሁኑ ወቅት በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች በሳይንስና በቴክኖሎጂ የታገዙ እንዲሆኑ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑንም አክለዋል። ዐውደ-ርዕዩ የፈጠራ ውጤቶችን ወደ ተግባር በመቀየር የሀገርን ብልጽግና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጉዞ እንደሚያፋጥን ታምኖበታል ነው ያሉት።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዘላለም ሙላቱ (ዶ/ር) እንደገለጹት መድረኩ ተማሪዎች ዕውቀት የሚያገኙበት ብቻ ሳይሆን፤ የጥበብ ባለቤት መሆናቸውን በተግባር የሚያሳዩበት ነው። ባለፉት ዓመታት ጥቂት ተማሪዎች ይሳተፉበት የነበረው የምርምርና ፈጠራ ሥራ ዛሬ የብዙዎች ባህልና ጉጉት መሆኑን መድረኩ ማረጋገጡንም ጠቁመዋል። ይህ የፈጠራ እድገት በከተማዋ በስፋት ከሚከናወኑ መሠረተ-ሰፊ የልማት ሥራዎችና ፕሮጀክቶች ጋር በጥብቅ የተሳሰረ መሆኑንም አብራርተዋል።   የቅድመ-1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በዓይነትና በጥራት መስፋፋታቸው ሕፃናት በራስ የመተማመን ስሜት ትምህርታቸውን እንዲጀምሩና ለሳይንስ ሥራዎች ጠንካራ መሠረት እንዲጥሉ እያደረገ ነው ብለዋል።
በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር የተሰማሩ ወጣቶች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ነው
Apr 24, 2026 115
ጎንደር፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በጎንደር ከተማ በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር በወተት ሀብት ልማት የተሰማሩ ወጣቶች ሀብትና ጥሪት በማፍራት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደግ መቻላቸውን ተናገሩ።   ወጣት አስናቀ አብተው ለኢዜአ እንደገለጸው፤ በሁለት ላሞች የጀመረውን የወተት ሀብት ልማት ሥራ ይህን አሃዝ አሁን ወደ 17 አሳድጓል። የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብሩ ሠርቶ መለወጥ የሚለውን ህልሜን ለማሳካት ረድቶኛል፤ በአሁኑ ወቅትም ለዘጠኝ ሰዎች የሥራ ዕድል ፈጥሬያለሁ ብሏል። በቀን ከ200 ሊትር በላይ ወተት ለገበያ በማቅረብም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ማሳደጉን ጠቅሷል።   በቀን ከ100 ሊትር በላይ ወተት ለገበያ በማቅረብ ላይ የሚገኘው ወጣት ዓለሙ ሲሳይ በበኩሉ፤ በአንዲት ላም የጀመረውን የወተት ሃብት ልማት ሥራ በአሁኑ ወቅት ወደ ሥድስት የሚታለቡ ላሞች ከፍ አድርጓል። የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር የአካባቢ ጸጋዎችን ለይቶ በመጠቀም ከራስ አልፎ ለሌሎችም የሥራ ዕድል በመፍጠር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያሳድግ መሆኑን በተግባር ማረጋገጡንም ገልጿል።   መርሐ-ግብሩ የወጣቱን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በተጨባጭ የሚያረጋግጥና በአጭር ጊዜ ሠርቶ መለወጥ እንደሚቻል የሚያመላክት የተግባር ትምህርት ቤት ነው ያለው ደግሞ ወጣት አምሳሉ አካሌ ነው፡፡ በወተት ሀብት ልማት ዘርፍ በመሰማራት ከአራት ላሞቹ የሚያገኘውን የወተት ምርት እሴት ጨምሮ ለገበያ በማቅረብ ራሱንና ቤተሰቡን በተሻለ መንገድ ማኖር እንደቻለም ነው ያመለከተው።   የጎንደር ከተማ አሥተዳደር እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ መላኩ ደምሌ፤ ባለፉት ሶስት ዓመታት ተግባራዊ የተደረገው የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር ለወጣቱ ሰፊ የሥራ እድል ለመፍጠር አስችሏል ብለዋል፡፡ የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችንና ግብዓቶችን በመጠቀም የወተት ምርትን በማሳደግ በኩል 12 ቴክኒሻኖችን በማሰልጠን ከ14 ሺህ በላይ ላሞችን የማዳቀል ሥራ መከናወኑንም አብራርተዋል። በወተት ሀብት ልማት ዘርፍ የሚታየውን የእንስሳት መኖ እጥረት ለማቃለል እንዲቻልም በሰአት 30 ኩንታል የእንስሳት መኖ ማዘጋጀትና ማቀናበር የሚችል ዘመናዊ ፋብሪካ ማቋቋም መቻሉን አስረድተዋል፡፡   በከተማው በወተት ሀብት ልማት፣ በንብ ማነብ፣ በዶሮ እርባታና በእንስሳት ማድለብ እንዲሁም በዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ በክላስተር የተደራጁ ከ25 በላይ ኢንተርፕራይዞች ተቋቁመው ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመዋል።፡
ለዜጎች በርካታ የሥራ ዕድል እየፈጠረ የሚገኘው አምራች ኢንዱስትሪ
Apr 24, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በአምራች ኢንዱስትሪዎች በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ከመሆናቸው ባሻገር ዕውቀትና ክኅሎታቸውን እያሳደጉ መሆኑን በተለያዩ ፋብሪካዎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ወጣቶች ገለጹ፡፡ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ትኩረት ከሰጣቸው ዋና ዋና ዘርፎች መካከል የአምራች ኢንዱስትሪውን ዐቅም ማሳደግ አንዱ ነው።   ይህም በዋናነት የውጭ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የውጭ ምንዛሪን ለማዳን ያለመ ነው። ይህንን ተከትሎ በተከናወነው ተግባር ከዚህ ቀደም ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ይወጣባቸው የነበሩ ምርቶች በሀገር ውስጥ እንዲመረቱ በማድረግ ረገድ ተጨባጭ ውጤቶች እየተመዘገቡ ይገኛሉ። በተለይም ተኪ ምርቶችን በስፋት በማምረት ለሀገር ውስጥ ገበያ ከማቅረብ ባለፈ፤ ወደ ውጭ በመላክ ተጨማሪ የውጭ ምንዛሪ ከማግኘት አንጻር ከፍተኛ ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል። አምራች ኢንዱስትሪው ለወጣቶችና ለሴቶች ሰፊ የሥራ ዕድል እየፈጠረ ሲሆን፤ የቴክኖሎጂና የዕውቀት ሽግግር እንዲኖር በማድረግ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ በማሻሻል ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተም ይገኛል፡፡ ኢዜአ በተለያዩ ኢንዱስትሪዎች በመዘዋወር ያነጋገራቸው የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ተጠቃሚዎች እንዳሉት፤ በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል ተጠቅመው ኑሯቸውን እየለወጡ ነው።   በጎበዝ ማኑፋክቸሪንግ ኤሌትሪክ ኢንዱስትሪ የምትሠራው ቅድስት አስማማው እንዳለቸው፤ በተፈጠረላት የሥራ ዕድል ገቢ ከማግኘቷ በተጨማሪ ክኅሎቷን እያሳደገላት ይገኛል። ሌላኛው የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ታምራት ተሰማ በበኩሉ፤ የአምራች ኢንዱስትሪዎች መስፋፋትን ተከትሎ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ከማድረጉ በተጨማሪ የዕውቀትና ቴክኖሎጂ ሽግግርን በማሳለጥ ረገድ ትልቅ ድርሻ እንዳለው ተናግሯል።   ይህንንም ተከትሎ ከዚህ በፊት በሌሎች ኢንዲስትሪዎች ከነበረው ልምድ አሁን ላይ በተሻለ ቴክኖሎጂ ራሱን ብቁ ማድረግ አንስቶ በፋብሪካው በሚከፈለው ክፍያ ራሱን ከማስተዳደር አልፎ ቤተሰብም እየደገፈ እንደሚገኝ ገልጿል፡፡ በዳቼ ማኑፋክቸሪንግ የምግብ ማቀነባበሪያ ፋብሪካ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ የሆነው እዮብ ዱሬሳ በበኩሉ በድርጅቱ የሥራ ልምድ ማግኘት መቻሉን ገልጾ፤ በሚከፈለው ክፍያም ከራሱ አልፎ ቤተሰቦቹን መደገፍ መቻሉን ተናግሯል፡፡   በዚሁ ፋብሪካ በተፈጠረላት የሥራ ዕድል የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቷ ማደግ እንደቻለ የገለጸችው ደግሞ ሌላኛዋ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ አሚራ ጀማል ናት።   በሁዋጃን ልዩ ኢኮኖሚክ ዞን የጎበዝ የፀሐይ ኃይል ሶላር ሴል ማምረቻ ሥራ አስኪያጅ በረከት ኃይሉ፤ መንግሥት ለኢንዱስትሪ ዘርፉ በፈጠረው ምቹ ምኅዳር ምርታቸውን ለተለያዩ ሀገራት እየላኩ መሆኑን ተናግረዋል።   በመንግሥት እየተደረገ ያለው ድጋፍ የማምረት ዐቅማቸውን እንዳሳደገውም ገልጸዋል። ድርጅቱ ከ600 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩንም አስረድተዋል። የዳቼ የምግብ ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ፕላንት ማኔጀር ዐቢይ በቀለ በበኩላቸው፤ ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት ትልቅ ዕድል እየፈጠረላቸው መሆኑን ይናገራሉ፡፡   መንግሥት በየጊዜው በሚያደርግላቸው ድጋፍና ክትትል ምርቶቻቸውን በጥራትና በፍጥነት በማምረት ወደገበያ ተዳራሽ ለማድረግ እንዳስቻላቸውም አንስተዋል። አሁን ላይ ድርጅቱ በአራት ፋብሪካዎች 46 ዓይነት የታሸጉ ምግቦችን እያመረተ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እያቀረበ መሆኑንም አረጋግጠዋል። ፋብሪካው ሥራ ሲጀምር በ40 ሠራተኞች ብቻ መጀመሩን አውስተው፤ መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረትም ውጤታማ መሆን በመቻሉ አሁን ላይ ከ1 ሺ 300 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ተናግረዋል፡፡
በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ ቀርቧል  
Apr 24, 2026 102
ጅማ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ተናገሩ። ኃላፊው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የሚመረተው የቡና ምርት ጥራቱን በጠበቀ መልኩ ለገበያ እየቀረበ ነው፤ አቅርቦቱም በየዓመቱ እያደገ መጥቷል። ለአርሶ አደሩ በየጊዜው የሚደረገው ድጋፍ፣ ክትትልና ሥልጠና የቡና ጥራትን በተሻለ ሁኔታ መጠበቅ እንዳስቻለም ገልጸዋል። ዘንድሮ 300 ሺህ ቶን የቡና ምርት መሰብሰቡን ገልጸው፤ ከዚህ ውስጥ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለሀገር ውስጥና ለውጪ ገበያ ማቅረብ ተችሏል ብለዋል።   ጥራት ያለው ቡናን ለገበያ በማቅረብ ሂደት ውስጥ መሠረታዊ የኅብረት ሥራ ማኅበራት ድርሻ የላቀ መሆኑንም አመላክተዋል። የጅማ ዞን የኅብረት ሥራ ማኅበራት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ድማሙ ንጋቱ በበኩላቸው፤ በዞኑ 1 ሺህ 300 መሠረታዊ የኅብረት ሥራ ማኅበራትና 4 ዩኒየኖች እንደሚገኙ ገልጸዋል። በቡና ምርት ላይ የተሰማሩ ዩኒየኖች በቡና ጥራትና አቅርቦት ላይ በትኩረት እየሠሩ መሆኑን ተናግረዋል። ዘንድሮ 4 ሺህ 800 ቶን የታጠበና ስፔሻሊቲ ቡና ለዓለም ገበያ ለማቅረብ ታቅዶ፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የዕቅዱን 60 በመቶ ማቅረብ መቻሉን አረጋግጠዋል።
ከአፍሪካ አቪዬሽን መሪነት እስከ አህጉራዊ የኢኮኖሚ ትስስር
Apr 23, 2026 226
በሙሴ መለሰ ኢትዮጵያ በአፍሪካ የአቪዬሽን ታሪክ ታይቶ የማይታወቅና በአህጉሪቱ ትልቁ የሆነውን የ12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ግዙፍ የኤርፖርት ግንባታ ፕሮጀክት በቢሾፍቱ ከተማ በይፋ መጀመሯን የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስታውቋል። ጋዜጠኛ ዳንኤል ኦሊቫሬስ ጋሌጎ በሲኤንኤን የጉዞ ገጽ ላይ ባሰፈረው ጽሁፍ እንደገለጸው፣ ይህ ሜጋ ፕሮጀክት አፍሪካውያን ተጓዦች ከአህጉሩ ውጭ ባሉ እንደ ዱባይ፣ ፓሪስና ለንደን ባሉ ማዕከላት በኩል የሚያደርጉትን አድካሚ ጉዞ በማስቀረት፣ አዲስ አበባን የአህጉሪቱ ቀዳሚ የመገናኛ ማዕከል ለማድረግ ያለመ ነው። ከአዲስ አበባ ከተማ በስተደቡብ ምስራቅ 48 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው ይህ ግዙፍ ግንባታ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ታሪክ ትልቁ የአቪዬሽን መሰረተ ልማት ተብሎ መጠቀሱን ጋዜጠኛው በዚሁ ጽሁፉ አመልክቷል።   ስራው በይፋ የተጀመረው ባለፈው ጥር ወር ሲሆን፣ አውሮፕላን ማረፊያው በ2023 ዓ.ም (2030 እ.ኤ.አ) የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታው ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር፣ በዓመት 60 ሚሊዮን መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም እንደሚኖረው በሲኤንኤን የጉዞ ገጽ ላይ ተመልክቷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው ለጋዜጠኞች በሰጡት ማብራሪያ፣ ፕሮጀክቱ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ በዓመት እስከ 110 ሚሊዮን መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል። ይህም አውሮፕላን ማረፊያውን በዓለም ላይ በርካታ ተጓዦችን ከሚያስተናግደው የአትላንታው ሀርትስፊልድ-ጃክሰን አውሮፕላን ማረፊያ ካለው አቅም በላይ እንደሚያደርገው ዳንኤል ኦሊቫሬስ ጋሌጎ ባሰፈረው ጽሁፍ አብራርቷል። አውሮፕላን ማረፊያው ከመንገደኞች አገልግሎት ባለፈ፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠናን (AfCFTA) በላቀ ሁኔታ ለመደገፍ ታቅዶ የተገነባ መሆኑን ጋዜጠኛው በሲኤንኤን የጉዞ ገጽ ላይ ባሰፈረው ጽሁፍ በዝርዝር አስቀምጧል።   በዓመት 3 ነጥብ 73 ሚሊዮን ቶን ጭነት የማስተናገድ አቅም ያለው ይህ መሠረተ ልማት፣ በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ የመጣውን የአፍሪካን የጭነት በረራ ፍላጎት በሚገባ ምላሽ መስጠት የሚችል መሆኑን ተጠቁሟል። የአውሮፕላን ማረፊያው የተርሚናል ዲዛይን በዓለም አቀፍ ደረጃ ዝነኛ በሆነው ዛሃ ሃዲድ አርክቴክትስ የቀረበ መሆኑን የጠቀሰው ጋዜጠኛው፣ዲዛይኑ የኢትዮጵያን ታላቁ ስምጥ ሸለቆና የተለያየ መልክዓ ምድራዊ ውበትን የሚያንፀባርቅ መሆኑን በጽሁፉ አካቷል። ተጓዦች በአውሮፕላን ማረፊያው ውስጥ ሲዘዋወሩ የኢትዮጵያን ባህልና ተፈጥሮ እንዲመለከቱ በሚያስችል መልኩ የተዘጋጀ ሲሆን፣ለዘላቂነት ቅድሚያ በመስጠት የፀሐይ ብርሃን ኃይልንና የዝናብ ውሃ አሰባሰብ ስርዓትን እንዲጠቀም ተደርጎ ተቀርጿል።   በአጠቃላይ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ መጠናቀቅ፣ኢትዮጵያ በአፍሪካ አቪዬሽን ያላትን መሪነት ከማረጋገጡ ባለፈ የአህጉሪቱን የኢኮኖሚ ትስስር ወደ አዲስ ምዕራፍ እንደሚያሸጋግረው ጋዜጠኛው በሲኤንኤን የጉዞ ገጽ ላይ ባሰፈረው ጽሁፍ ደምድሟል። ይህ ፕሮጀክት ከሌሎች የአፍሪካ አየር መንገዶች ጋር በመተባበር የነጠላ የአፍሪካ አየር ትራንስፖርት ገበያን (SAATM) ወደ ተግባር ለመቀየር የሚደረገውን ጥረት በእጅጉ እንደሚያግዝም ተመልክቷል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ኤክስፖዎች የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የማምረት ዐቅምና የእርስበርስ ትስስር እያጠናከሩ ነው
Apr 23, 2026 110
ድሬዳዋ፤ ሚያዝያ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚዘጋጁ ኤክስፖዎች የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የማምረት ዐቅምና የእርስበርስ ትስስር በማጠናከር ተወዳዳሪነትን ለማላቅ መደላድል እየፈጠሩ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ገለጸ። ድሬ ታምርት፤ ኢትዮጵያ ትበልጽግ በሚል መሪ ሐሳብ በድሬዳዋ የተዘጋጀ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ኤክስፖ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተከፍቷል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በዚሁ ወቅት፤ ኤክስፖዎች የአምራች ኢንዱስትሪዎች የምርት ጥራትና ደረጃን በማሟላት ረገድ የደረሱበትን ከፍታ ለማሳየትና ለሚስተዋሉ ክፍተቶች ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት እያገዙ መሆኑን ተናግረዋል።   በተጨማሪም የእርስበርስ ትስስርን፣ መመጋገብንና ውድድርን በማጠናከር ሀገራዊ ትልምን ከዳር ለማድረስ ምቹ መደላድል እየፈጠሩ መሆኑን አስረድተዋል። ከሚያዝያ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ሀገር አቀፍ ኤክስፖ እንደሚዘጋጅም ጠቁመዋል። በኤክስፖው ላይ ምርታቸውን ያቀረቡ የአምራች ኢንዱስትሪ ተወካዮች በበኩላቸው፤ የግብዓት ልውውጥና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ኤክስፖዎች መዘጋጀታቸው ለአምራች ኢንዱስትሪው ወሳኝ አበርክቶ እንዳላቸው ገልጸዋል። ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎቹ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በተደረገላቸው ድጋፍ ወደ ማምረት የተሸጋገሩ አዳዲስ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ጎብኝተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም