ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በክልሉ በፍራፍሬና በቡና ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል − ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
May 24, 2026 116
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ) ፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በፍራፍሬ እና በቡና ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ በክልሉ በፍራፍሬ፣ በቡናና ሥራስር ተክሎች ልማት ለሀገር ውስጥ እና ለውጪ ገበያ ለማቅረብ የተከናወኑ ሥራዎች ውጤት ተገኝቶባቸዋል። በዚህም ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑና ለውጪ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶች ላይ ይበልጥ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በበጋ መስኖና በመኸር እርሻ ከ107 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በፍራፍሬና በአትክልት መሸፈኑን ተናግረዋል። በዋናነትም ሙዝ፣ ማንጎ፣ አቮካዶ እና የደጋ ፍራፍሬ እንዲሁም የተለያዩ የጓሮ አትክልቶች መልማታቸውን ርዕሰ መስተዳድሩ ጠቁመዋል። ከሀገራዊ ለውጡ በፊት በክልሉ ከ60 ሺህ ሄክታር ያልበለጠ የሙዝ ማሳ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ጥላሁን፣ በአሁኑ ወቅት በአራት እጥፍ አድጎ ከ240 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት መልማቱን ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር ለፍራፍሬ ልማት ሽፋን እያደገ መምጣት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም ገልጸዋል። እንደ አቶ ጥላሁን ገለጻ በተያዘው ዓመት በፍራፍሬ የሚለማውን መሬት ሽፋን ለማሳደግ በተያዘ ዕቅድ በተለያዩ አካባቢዎች የሚተከሉ ከ25 ሚሊዮን በላይ የአቮካዶ፣ ማንጎ እና አፕል ችግኞች ተዘጋጅተዋል። በማህበር የተደራጁ ወጣቶችም በፍራፍሬ ልማት፣ በግብይትና ማቀነባበር የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸው ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ነው የገለጹት። የቡና ልማትን ከማስፋፋት አንጻር ለቡና ምቹ በሆኑ ሁሉም የክልሉ አካባቢዎች ልማቱ እየተከናወነ መሆኑን ያመለከቱት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በጌዴኦ ዞን ቡናን ስፔሻላይዝድ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። የቡና ልማቱን በጥምር ግብርና በማከናወን የአርሶ አደሩን ዘርፈ ብዙ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራትም ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። በክልሉ የቡና ልማቱን ለማስፋት በተያዘው ዕቅድ መሰረት ዘንድሮ ከተዘጋጁ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና ችግኞች አብዛኞቹ ባለፈው ሚያዝያ ወር መተከላቸውን ገልጸው፣ ቀሪዎቹ በቀጣይ ሐምሌ ወር ይተከላሉ ብለዋል።
በአማራ ክልል የግብርናውን ክፍለ ኢኮኖሚ የሚያጠናክሩ ተግባራት ትኩረት የተሰጣቸው ናቸው- ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
May 24, 2026 87
ጎንደር ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የግብርናውን ክፍለ ኢኮኖሚ የሚያጠናክሩ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ አስታወቁ ። የጎንደር የተቀናጀ አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ የግንባታ ማስጀመሪያ ስነ ስርዓት በጎንደር ዙሪያ ወረዳ ዛሬ ተካሂዷል ። ርእሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንደገለጹት በክልሉ የግብርናውን ዘርፍ ኢኮኖሚያዊ እድገት የሚያጠናክሩና የሚያሳልጡ ተግባራት ትኩረት የተሰጣቸው ናቸው ። በክልሉ ግንባታው የተጀመረው የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ የዚሁ አካል መሆኑን ጠቁመው ፓርኩ በክልሉ ዋነኛ የኢኮኖሚ ማእከል እንደሚሆንም አመልክተዋል ። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በበኩላቸው በሀገሪቱ ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ የሚደረገውን መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር በማፋጠን ረገድ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ወሳኝ የእድገት ምሰሶዎች ናቸው ብለዋል። የተቀናጀ የአግሮ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የግብርና ምርት እሴት ጨምሮ ለሀገርና ለውጪ ገበያ ለማቅረብ ምቹ የኢኮኖሚ መሠረት የሚጥሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። ዛሬ ግንባታው የተጀመረው አግሮ ኢንዱስትሪ ፓርክ የአካባቢውን የግብርና ምርት በስፋት በመጠቀም ለአካባቢው አምራች አርሶ አደሮች ሰፊ የገበያ እድል የሚፈጥር እንደሆነም አመልክተዋል። ፓርኩን በሂደት ወደ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን በማሳደግ እንደ ሀገር ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ የሚደረገውን ሽግግር ለማሳለጥ ምቹ መደላድል የሚፈጥር መሆኑን ጠቅሰዋል። ፓርኩ ለግብርና ምርቶች የገበያ እድል በማመቻቸት ለወጣቶች ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር እንዲሁም ለከተሞች ገቢ ማደግና ለቴክኖሎጂ ሽግግር የላቀ አስተዋጽኦ እንዳለውም ጠቁመዋል። የአማራ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ብርሀኑ ጣምያለው ኢንዱስትሪ ፓርኩ በ256 ሄክታር መሬት ላይ ግንባታው እንደሚካሄድ ገልጸዋል። የፓርኩ ግንባታ ከ8 ቢሊዮን ብር በላይ የኢንቨስትመንት ወጪ እንደሚጠይቅ ጠቁመው ስራ ሲጀምር ለ55 ሺህ ወገኖች ቋሚ እንዲሁም ከ200ሺህ በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎች ጊዚያዊ የስራ እድል ይፈጥራል ብለዋል። ፓርኩ በአመት ከአንድ ሚሊዮን ቶን በላይ ምርት የማቀናበር አቅም ሲኖረው እሴት የተጨመረባቸውን ምርቶች ለውጪ ገበያ በማቅረብ የውጪ ምንዛሪ የሚያስገኝ መሆኑንም አስታውቀዋል። የማእከላዊ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አወቀ አስፈሬ ዞኑ ለአግሮ ኢንዱስሪዎች ግብአት የሚውል ሰሊጥ፣ አኩሪ አተርና ጥጥ የመሳሰሉ የግብርና ምርቶች በስፋት የሚመረቱበት እንደሆነ ተናግረዋል ። ኢንዱስትሪ ፓርኩ ለአካባቢው የኢኮኖሚ መነቃቃት አስተዋፅኦው የላቀ መሆኑንም አመልክተዋል። በኢንዱስትሪ ፓርኩ የግንባታ ማስጀመሪያ ስነ ስርአት ላይ የፌደራል፣ የክልል እንዲሁም የጎንደር ከተማና የማእከላዊ ጎንደር ዞን አመራሮችና የአካባቢው ማህበረሰብ ተገኝተዋል።
በሐረሪ ክልል አቮካዶን በተሻለ ደረጃ በማምረት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማጎልበት ወደ ስራ ተገብቷል
May 24, 2026 82
ሐረር፣ ግንቦት 16/2018(ኢዜአ):- በሐረሪ ክልል የአቮካዶ ልማትን በተሻለ ደረጃ በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማጎልበት ወደ ስራ መገባቱን የክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ አስታወቀ። በኢትዮጵያ ከፍተኛ የገበያ ተፈላጊነት ያላቸውንና አምራች አርሶ አደሮችን በአጭር ጊዜ ተጠቃሚ የሚያደርጉ እንደ አቮካዶ ያሉ ከፍተኛ እሴት ያላቸው አትክልትና ፍራፍሬ ልማቶች በስፋት እየተስፋፉ ይገኛሉ። የሐረሪ ክልልም ያለውን የተወሰነ የእርሻ መሬት በቴክኖሎጂ በማገዝ ምርታማነትን ለመጨመርና የአካባቢውን ማህበረሰብ የውስጥ ፍጆታ ከመሸፈን ባለፈ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ያቀደውን ስራ ስኬታማ ለማድረግ፣ የአመራሩና የባለሙያው አቅም መገንባት ወሳኝ መሆኑ ይገለጻል። በክልሉ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ለማስጀመር በልማቱ ዙሪያ ለዘርፉ አመራሮች፣ ባለሙያዎችና ባለድርሻ አካላት ስልጠና በመሰጠት ላይ ይገኛል። በመድረኩ የተገኙት የክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ነስረዲን አህመድ ለኢዜአ እንዳሉት በክልሉ ከአረንጓዴ አሻራ ልማት ጋር በማያያዝ አቮካዶን የማልማት ስራ እየተከናወነ ነው። ይህንን ተግባር ለማጎልበት በክልሉ በብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም የተለያዩ ስራዎች ተቀርጸው ተግባራዊ የማድረግ ስራ መጀመሩን ተናግረዋል። በዚህም የአቮካዶ ልማት የሚከናወንበት ቦታን የመለየት ስራ መከናወኑን የተናገሩት አቶ ነስረዲን በክልሉ በአራቱ የገጠርና ከተማ ወረዳዎች ውስጥ ተግባራዊ እንደሚደረግ ተናግረዋል። በተለይም የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ የአቮካዶ ልማት የዝግጅት ስራዎች አንዱ መሆኑን ጠቁመው ችግኝ የማፍላትና የማዳቀል እንዲሁም የአርሶ አደሮችን ግንዛቤ የማሳደግ ስራዎች መከናወናቸውን አብራርተዋል። ይህ የአቮካዶ ልማት ኢንሼቲቭ በቴክኖሎጂ በማዘመን አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ማድረግ፣ ምርቱን ለዓለም አቀፍ ገበያ በማቅረብ የውጭ ምንዛሬን ማሳደግ እንዲሁም በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እገዛ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። የሐረሪ ክልል አየር ፀባይ ለአቮካዶ ልማት ምቹ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ መሐመድ ሬድዋን ናቸው። ይህ ፕሮግራም በክልሉ ምርትና ምርታማነትን በማጎልበት የአርሶ አደሩን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ሥራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር ትልቅ እገዛ ከማድረጉ ባለፈ ለወጣቶችም የስራ እድል ይፈጥራል ብለዋል።
በዲላ ከተማ የተዘጋጀው "ቡኖ - ማላ" ኤክስፖ ምርቶችንና የኢንቨስትመንት እድሎችን ለማስተዋወቅ አስችሏል
May 24, 2026 96
ዲላ፤ ግንቦት 16/2018 (ኢዜአ)፡-ከ40 በላይ የንግድ ተቋማትና አጋር አካላት ተሳትፈውበት በዲላ ከተማ የተዘጋጀው "ቡኖ - ማላ" ኤክስፖ ምርቶችን እና የኢንቨስትመንት እድሎችን ጭምር ለማስተዋወቅ መልካም እድል መሆኑ ተገለጸ። ለሁለት ተከታታይ ቀናት የሚካሄደውን "ቡኖ - ማላ" ዓለም አቀፍ ኤክስፖ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት የልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ኢንጂነር ስለሺ ኮሬ (ዶ/ር) በይፋ ከፍተውታል። በዚሁ ጊዜ ባስተላለፉት መልዕክትም በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም በቁም እንስሳት ሃብት የሚታወቀው የጌዴኦ ዞን ምርታማነቱ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በቡና እና ሌሎችም የልማት መስኮች የተሰማሩ ከ40 በላይ የንግድ ተቋማትና አጋር አካላት የተሳተፉበት ዓለም አቀፍ ኤክስፖ መሆኑ ትልቅ ትርጉም አለው ብለዋል። በመሆኑም ኤክስፖው ምርትና አገልግሎትን እንዲሁም የኢንቨስትመንት እድሎችን ጭምር ለማስተዋወቅ መልካም ዕድል መሆኑን ተናግረዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡናና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አማኑኤል ብሩ፤ በክልሉ የይርጋጨፌ፣ የኮቾሬና አማሮን ጨምሮ ሌሎችም አካባቢዎች የባለ ልዩ ጣዕም ቡና የሚመረትባቸው መሆናቸውን አንስተዋል። ቡናን በጥሬ ከመላክ ባለፈ በልዩ ጣዕሞች አዘጋጅቶ እሴት ጨምሮ በመላክ መልካም ጅምሮች መኖራቸውን አንስተው፣ ኤክስፖው ጥሩ ተሞክሮ ለመቀመርና ምርቶችን ለማስተዋወቅ የጎላ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በዞኑ በግብርና ልማት በተለይም በቡና፣ እንሰትና የቁም እንስሳት ሃብት እምቅ አቅም መኖሩን አንስተው ኤክስፖው ይህንኑ ይበልጥ ለማስተዋወቅ መልካም ዕድል ነው ብለዋል። የጌዴኦ ዞን የባህላዊ መልከዓ ምድር ማዕከል መሆኑን አንስተው በሆቴልና ቱሪዝም ዘርፍ ለሚሰማሩ አካላት አዋጭ የገበያ ዕድል እንዳለም ተናግረዋል። በዞኑ ከ80 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቡና የተሸፈነ መሆኑን የገለጹት ዋና አስተዳዳሪው፣ የተለያየ ደረጃ ያላቸው የቡና ምርቶችንም ወደተለያዩ የወጭ ሀገራት እንደሚላኩ ተናግረዋል። የይርጋጨፌ ቡና ገበሬዎች ሕብረት ሥራ ዩኒየን ተወካይ ቤተልሔም ዳንኤል፤ ዩኒየኑ ጥራቱን የጠበቀ ጥሬ ቡና ለውጭ ገበያ ከማቅረብ ባለፈ የውጭ ገዥዎችን መሰረት ያደረገ እሴት የተጨመረበት ቡና ለገበያ እያቀረበ መሆኑ አንስተዋል። በተለይ በቀን ከዘጠኝ ኩንታል በላይ በራሱ ልዩ ጣዕም ተቆልቶና ተፈጭቶ የተዘጋጀ ቡና ለገበያ በማቅረብ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን አንስተው፣ በኤክስፖውም ተጨማሪ የገበያ ትስስር እየፈጠሩ መሆኑን ተናግረዋል። በቡና ንግድ በእሴት ሰንሰለቱ ያሉ ተዋንያንን መቀነስ ለትርፋማነት መሰረት መሆኑን ያነሱት ደግሞ ወልትአብንዶ የቡና አቅራቢ ማህበር ሰብሳቢ ወይዘሮ ሽታዬ ሃጥያ ናቸው።
በኦሮሚያ ክልል የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ለማቀላጠፍ የአሰራር ማሻሻያና ለተቋማት ግንባታ ትኩረት ተሰጥቷል
May 24, 2026 134
አዳማ፤ግንቦት 16/2018(ኢዜአ)፦በክልሉ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ለማቀላጠፍ ለአሰራር ማሻሻያና ለተቋማት ግንባታ ትኩረት መሰጠቱን በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ ገለፁ። በክልሉ ምስራቅ ሸዋ ዞን በቴክኖሎጂ የተደራጀ የአስተዳደር ህንፃ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ በወቅቱ እንደገለፁት፥ የክልሉ መንግሥት የአገልግሎት አሰጣጥ ለማቀላጠፍ የአሰራር ማሻሻያና በተቋማት ግንባታ ላይ በትኩረት እየሰራ ነው። የህዝቡን የልማት ጥያቄዎችና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በቅርበት ለመፍታት የቀበሌ አደረጃጀትን በቅርበት በመዘርጋት የአገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን ላይ መሰራቱን አስታውሰዋል። ይህም ህዝቡ አገልግሎቱን በቅርበት በማግኘት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማቱን እንዲያፋጥን ከማስቻሉም በላይ የመልካም አስተዳደር ቅሬታዎችን መፍታት መቻሉን አመልክተዋል። የተገልጋይን እርካታ ለማሳደግም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነት ላይም በስፋት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስም ባለፉት አምስት ዓመታት ከተሰሩት ከ90ሺህ በላይ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሰረተ ልማቶች ውስጥ 70 በመቶ የሚሆኑት በህዝብ ተሳትፎ መሰራታቸውን ተናግረዋል። የምስራቅ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባቡ ዋቆ በበኩላቸው፥ ዞኑ የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን ለማቀላጠፍ ሴክተር መስሪያ ቤቶችን ወደ አንድ ማእከል የማምጣትና በቴክኖሎጂ የማደረጀት ተግባር ማከናወኑን አንስተዋል። የዚሁ አካል የሆነው አዲሱ የዞኑ አስተዳደር ህንፃም ለተገልጋዮች ምቹ ከመሆኑ ባለፈ አስተዳደሩ ያወጣ የነበረን ኪራይ መቅረፍ እንደሚያስችል ጠቁመዋል። ይህም 17 መስሪያ ቤቶችን በአንድ ላይ የያዘ ከመሆኑም ባለፈ ከወረዳዎች ጋር በቴክኖሎጂ የተያያዘ መሆኑን ተናግረዋል። ህንፃው ቤተ መጻሐፍት፣ የመሰብሰቢያ አዳራሾች፣ የህፃናት ማቆያ፣ የተሽከርካሪ ማቆሚያና ሌሎችን የያዘና በዲጂታል ቴክኖሎጂ የተደራጀ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። በዚህም የዲጂታል አገልግሎት ለማቀላጠፍ የሚያስችል ምቹ የመስሪያ ቦታ መገንባቱን ገልጸዋል። በምረቃው ፕሮግራም ላይ የፌዴራልና የክልሉ መንግሥት የስራ ሃላፊዎች፣ አባገዳዎችና ሃደ ሲንቄዎች እንዲሁም ከዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የተውጣጡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን የሚወስን ቁልፍ የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ ነው
May 23, 2026 586
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት የሀገርን ኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን የሚወስን ቁልፍ የብሔራዊ ጥቅምና የሕልውና ጉዳይ መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ገለጹ። ጥያቄው ታሪካዊነትን ከመልክዓ-ምድራዊነት፣ ሕጋዊነትን ደግሞ ከፍትሐዊ ተጠቃሚነት ጋር ያሰናሰለ ጠንካራና ምክንያታዊ መሠረት ያለው መሆኑን አስገንዝበዋል። ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያና የቀይ ባሕር ዳርቻ ትስስር በሀገረ-መንግሥት ምሥረታና ግንባታ ታሪክ ውስጥ እጅግ የጠበቀ ነው ብለዋል፡፡ ለአብነትም በአክሱም ሥልጣኔ ዘመን የነበረው ኃያልነትና በአዱሊስ ወደብ አማካኝነት ከመካከለኛው ምሥራቅ አገሮች ጋር የተደረገው ሰፊ የንግድ ልውውጥ ከቀይ ባሕር ቁርኝት የመነጨ እንደነበር አብራርተዋል። በታሪክ ሂደት ውስጥ ኢትዮጵያን ከቀይ ባሕር ለማራቅ የውስጥ ባንዳዎችን በማሰለፍ ጭምር የሸረቡት ሴራና የተሳሳተ ስሌት በእጅጉ የሚያስቆጭ የታሪክ ስብራት መሆኑን ጠቁመዋል። ዛሬም ቢሆን የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለማደናቀፍ የውጭ ኃይሎችና የእነርሱ ተላላኪ የሆኑ የሀገር ውስጥ ኃይሎች በተሳሳተ ስሌት እየተጓዙ መሆኑን አክለዋል። ባለፉት ሦስት አስርት ዓመታት የባሕር በር ጉዳይን ማንሳት እንደ ተንኳሽነት የሚቆጠርበትን አደገኛ ትርክት በመስበር፣ ወሳኝ የምክክርና የንግግር አውድ እንዲፈጠር መደረጉን ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ይፋ ካደርጉበት ጊዜ ጀምሮም የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በህዝብ ለህዝብ ግንኙነትና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ሥራዎች ማከናወኑን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያውያን በብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ ላይ የተደመረ ዕይታና ፅኑ አቋም ሊኖራቸው ይገባል ብለዋል። በምንም ዓይነት የፖለቲካ ልዩነት የትውልድን ጥያቄ አሳልፎ መስጠት እንደማይገባና ለብሔራዊ ጥቅምና ፍላጎት መከበር በትብብር መቆም እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የባሕር በር ፍላጎቷን በሰላማዊና በሰጥቶ መቀበል መርህ እያቀረበች መሆኑን በመጥቀስ፤ በዓለም አቀፍ ደረጃ የላቲን አሜሪካ ሀገራት ቦሊቪያና ፔሩ፣ ብራዚልና ፓራጓይ፤ በአፍሪካ የማሊ፣ ሴኔጋልና ኮትዲቯር የተጠቀሙባቸውን የጋራ መፍትሔዎች በተሞክሮነት አስረድተዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 መሠረት የኢኮኖሚ ውህደት የሰፈነባት አህጉር ለመፍጠር በቀጣናው ሀገሮች መካከል የኃይል ትስስር በመፍጠር የባሕር በር ፍላጎቷን በሰፊው እያስረዳች መሆኑንም ገልጸዋል። የባሕር በር አለመኖር በሀገር ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ጫና እያሳደረ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፤ በየዓመቱም ኢትዮጵያ ለወደብና ሎጂስቲክስ አገልግሎት ብቻ ከአንድ ነጥብ አምስት እስከ ሁለት ቢሊዮን ዶላር ወጪ ለማድረግ መገደዷን ተናግረዋል። ይህም በወጪና ገቢ ንግድ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት እንዲሁም በጠቅላላው የዕድገት ጉዞ ላይ ትልቅ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩን አስገንዝበዋል። በመሆኑም መገናኛ ብዙኃን ብሔራዊ መግባባትን በማጉላት፤ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ማስረዳት እንዳለባቸው ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ የኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነትን በማስከበር ዕድገትና ብልፅግና ከሚወስኑ ቁልፍ ብሔራዊ ጥቅም ጉዳዮች ውስጥ አንዱ ነው ብለዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የተገነባውን የተቀናጀ የከተማ ግብርና ማዕከል መረቁ
May 23, 2026 357
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የሚገኘውን የተቀናጀ የከተማ ግብርና ማዕከል መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በመልዕክታቸው፤ የተቀናጀ የከተማ የግብርና ማዕከሉ በ3 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ እና 18 ሱቆችን እንዲሁም 18 ሼዶችን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። አዲስ አበባ ለሁሉም የምትመች የጋራ ቤትና ልማቷም አካታች መሆኑን አመልክተዋል። ባለፈው ሥርዓት አርሶ አደሩ የሚገፋበት፣ መሬቱ ብቻ ተፈልጎ እርሱ የሚዘነጋበት የነበረ በመሆኑ ለለውጡ መምጣት ገፊ ምክንያት እንደነበር አስታውሰዋል። የአሁኑ የከተማ አስተዳደር አርሶ አደሩን በሁሉም የከተማ ልማት ውስጥ አካቶ አብሮ እንዲለማ እና ተጠቃሚነቱ እንዲረጋገጥ እያደረገ መሆኑን ከንቲባ አዳነች ገልጸዋል። አርሶ አደሩ ለልማት በሚነሳበት ወቅት ተገቢውን ካሳ ከማግኘት ባለፈ ከልማቱ ቀጥተኛ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደም በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ በ14 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተገነባው የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ልህቀት ማዕከል እና ዛሬ በለሚ ኩራ የተመረቀው ማዕከል የዚሁ ማሳያ መሆናቸውንም ነው ያብራሩት። እነዚህን መሰል ማዕከላት የከተማው ነዋሪ የሚያጋጥመውን የዋጋ ንረት ለመከላከል እና በተመጣጣኝ ዋጋ የግብርና ምርቶችን ለማቅረብ ያስችላሉ ያሉት ከንቲባዋ፣ አሰራሩ በጋራ ማደግንና ተባብሮ መበልጸግን የሚያሳድግ መሆኑን ገልጸዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ይህንን ግዙፍ ስራ በማቀድ፣ በማስተባበርና ውጤታማ እንዲሆን በማድረግ ረገድ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
በካፋ ዞን የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት አሳድገዋል
May 23, 2026 222
ቦንጋ ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦በካፋ ዞን ህብረተሰቡን በማሳተፍ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማሳደጋቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ፡፡ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በካፋ ዞን ሺሾእንዴ ወረዳ ከ44 ሚሊዮን ብር በላይ በሚሆን ወጪ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል። ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል ሞዴል ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት፣ የወሺ ፏፏቴ የቱሪስት መዳረሻ፣ ሞዴል ጤና ኬላ እንዲሁም የኖባ ሽመሮ እና ወሺ ጊዳ የመንገድ መሰረተ ልማት ይጠቀሳሉ። የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ እንደገለፁት፤ በዞኑ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት አሳድገዋል። ዛሬ የተመረቁ የተለያዩ ፕሮጀክቶችም የዚሁ ማሳያዎች ናቸው ያሉት አቶ እንዳሻው፣ በዞኑ በዚህ ዓመት ህብረተሰቡን በማሳተፍ የመሰረተ ልማት ችግሮችን ለመቅረፍ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በትምህርቱ ዘርፍ የሚስተዋለውን የጥራትና ውጤታማነት ችግር ለመፍታትም ሞዴል ቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችን ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። የጤና አገልግሎቶችን ተደራሽ ማድረግ ትኩረት የተሰጠው አንዱ ተግባር ነው ያሉት አስተዳዳሪው በዚህም የጤና ተቋማትን ከመገንባት ባለፈ አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የተሰራው ስራ ውጤት ማስመዝገቡን ነው የተናገሩት፡፡ የቱሪስት መዳረሻን በማልማት ረገድ ለወጣቶች ስራ ዕድል በመፍጠርና ቱሪስቶችን ለመሳብ በተደረገው ጥረት ዛሬ የተመረቀው የወሺ ፏፏቴ መዳረሻም የተደበቀውን እምቅ ሀብት አጉልቶ ያወጣ ነው ብለዋል። የሺሾእንዴ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ደምሴ ገብረማርያም በበኩላቸው፣ በወረዳው የህብረተሰቡ የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለሆኑ የመንገድ፣ የትምህርት፣ የጤናና ሌሎች መሰረተ ልማት ምላሽ ለመስጠት እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። በዛሬው እለት የተመረቁት መንገዶች አርሶ አደሩ ምርቱን ለገበያ እንዲያወጣ እንዲሁም በፍጥነት የጤና አገልግሎትን እንዲያገኝ ትልቅ አስተዋጽኦ ያለው ነው ብለዋል፡፡ የወረዳው ነዋሪዎችም ከዚህ ቀደም በአካባቢያቸው መንገድ ባለመኖሩ ምርታቸውን ወደ ገበያ ለማውጣትም ሆነ ወደ ጤና ተቋማት ፈጥኖ ለመድረስ ይቸገሩ እንደነበር ተናግረዋል። ዛሬ የተመረቁት የትምህርት፣ የመንገድና የጤና ተቋማት ለበርካታ ዓመታት ይነሱ የነበሩ ጥያቄዎችን የመለሱ መሆናቸውን አስረድተዋል።
በኦሮሚያ ክልል በለውጡ አመታት በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ከ43ሺህ በላይ ደርሰዋል -ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ
May 23, 2026 356
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ከለውጡ በፊት ከ10ሺህ በታች የነበረው የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች በለውጡ አመታት በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ከ43ሺህ በላይ መድረሳቸውን የክልሉ ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በሞጆ ከተማ የተገነባውን የግራንዴር ሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካን መርቀዋል። የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት የኦሮሚያ ክልልን የኢንቨስትመንት ማዕከል ለማድረግና የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሞተር እንዲሆን በትኩረት እየተሠራ ይገኛል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት የመደመር እሳቤን መሠረት በማድረግ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት ሰፊ ሥራ መሠራቱንም ገልጸዋል። በክልሉ ቡልቡላ እና ግንባታው በመጠናቀቅ ላይ የሚገኘው የነቀምቴ ኢንዱስትሪ ፓርኮችን እንዲሁም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ግንባታው የተጀመረውን ገዳ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን በዋቢነት አንስተዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በገዳ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ብቻ በአሁኑ ወቅት ከ70 በላይ ባለሃብቶች ወደ ኢንቨስትመንት ለመግባት በሂደት ላይ እንደሚገኙ እና ከ30 በላይ የሚሆኑት ደግሞ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ ደርሰዋል ብለዋል። የክልሉ መንግሥት ቢሮክራሲን በመቀነስ፣ አሠራሮችን በማሳለጥ፣ መሠረተ ልማቶችን በማሟላት እና ወጣቶች ክህሎት ይዘው የልማቱ ተሳታፊ እንዲሆኑ በማድረግ ምቹ የኢንቨስትመንት ከባቢን እየፈጠረ መሆኑንም አስታውቀዋል። የዛሬው የግራንዴር ሴራሚክ ፋብሪካ ምረቃም የዚሁ እንቅስቃሴ ውጤት አካል መሆኑን ነው የገለጹት። የግብርናው ዘርፍም ከተለመደው አሠራር ወጥቶ ወደ ኢንቨስትመንት እየተሸጋገረ መሆኑን ጠቁመው፣ በተያዘው መንገድ በቁርጠኝነት ከተሠራ የክልሉም ሆነ የሀገሪቱ ብልጽግና በአጭር ጊዜ እውን እንደሚሆን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው፤ ለቀጣናዊ ትስስር እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት የላቀ ሚና አለው
May 23, 2026 212
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ታሪካዊና ሕጋዊ መሰረት ያለው፤ ለቀጣናዊ ትስስር እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት የላቀ ሚና እንዳለው የዘርፉ ምሁራን አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ቀደም ሲል፤ የቀይ ባህር ጉዳይ ለኢትዮጵያ ሕጋዊ፣ ታሪካዊ፣ መልክዓ ምድራዊ (ጂኦግራፊያዊ) እና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄ መሆኑን መግለጻቸው ይታወሳል። ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችበት መንገድ ሕጋዊና ተቋማዊ መሰረት እንደሌሎው የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ኢትዮጵያና ቀይ ባህር ለዘለዓለም ተነጣጥለው ሊኖሩ እንደማይችሉና ጥያቄው በፍትሐዊ፣ በሰላማዊ፣ በሰጥቶ መቀበል መርህ ምላሽ እንዲያገኝ የሚደረገው ጥረት እንደሚቀጥል ማስታወቃቸው ይታወሳል። የኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የአመራርና አስተዳደር ኮሌጅ ምክትል ዲን መሀመድ አሊ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድና በቀጣናው ላይ ከፍተኛ የሰላም ማስከበር ሚና ስትጫወት የቆየችና አሁንም ይህንኑ እያደረገች ያለች ሀገር መሆኗን ገልጸዋል። በተለይም በሰላም ማስከበር የሰለጠነ የሰው ኃይል በማሰማራት፣ መስዋዕትነት ጭምር እየከፈለች የአካባቢውን ሰላምና ጸጥታ በማስከበር በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተች መሆኗን አብራርተዋል። ይህ የሰላም ማስከበር ልምዷ በቀይ ባህር ቀጣና ላይ ካላት ስትራቴጂካዊ ጥቅም ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት እንዳለውም ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ አጠቃላይ የወጪና ገቢ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መሰረት ያደረገው ቀይ ባህርን መሆኑን አመልክተው፤ በዚሁ ቀጣና ሀገሪቱ የተለየ ፍላጎትና ጥቅም ሊኖራት እንደሚገባ አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ወደ ባህር በር መመለስ ለጎረቤት ሀገሮችም ጭምር የጋራ ጥቅም እንዳለው የቀጣናው ሕዝቦች እንዲገነዘቡ ማድረግ ያስፈልጋል ያሉት ምሁሩ፤ አካባቢው ላይ አስተማማኝ ሰላምና ጸጥታ እንዲሰፍን ኢትዮጵያ ትልቁን ሚና እንደምትጫወት ተናግረዋል። ይህም ጠቃሚነቱ ለአንድ ሀገር ብቻ ሳይሆን ለሁሉም ጎረቤት ሀገሮች እንደሚሆን ማሰብ ይገባል ብለዋል። በቀጣናው የሚኖረው ማህበረሰብ በቋንቋ፣ በእምነት፣ በባህልና በኢኮኖሚ በከፍተኛ ደረጃ የተሳሰረ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህንን ቀጣናዊ ትስስር አጠናክሮ የመቀጠል ጥቅም አጠቃላይ የቀጣናው ሕዝብ እንዲገነዘበው የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን በማጠናከር በኩል በትኩረት መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ የዓለም አቀፍ ግንኙነት ረዳት ፕሮፌሰር ናርዶስ ሃዋዝ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የቀይ ባህር ጉዳይ ሁል ጊዜም ቢሆን የታሪካዊ ባለቤትነት ጥያቄን አብሮ የሚያስነሳ መሆኑን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነትን ለማረጋገጥ የምታደርገው ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ትልቁ ሚናውና ማጠንጠኛው ከዚሁ ታሪካዊ እውነታ ጋር የተያያዘ መሆኑን ገልጸዋል። በመንግሥታት ደረጃ የሚደረገው ዲፕሎማሲያዊ ንግግርና ውይይት እንደተጠበቀ ሆኖ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ድንበር ተሻጋሪ የሆኑ የሕዝቦች የጋራ ማንነት၊ ባህልና ታሪክ መኖሩንና በእነዚህ ሕዝቦች መካከል ባለው ትስስር ላይ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን በማጠናከር መቀራረብን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚገባ ተናግረዋል። ይህ የሕዝብ ለሕዝብ ትስስር ደግሞ ውሎ አድሮ ቀጣናውን በራሱ ጊዜ ወደ አንድ የተዋሃደ ማህበረሰብ ሊመራው እንደሚችልም አመልክተዋል።
የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ ለፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት ተገንብቷል
May 23, 2026 116
ሃዋሳ፤ ግንቦት 15/2028 (ኢዜአ)፡- የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ ለፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት መገንባት መቻሉን የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሃመድ ገለጹ፡፡ የመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽን ለመከላከያ ሰራዊት አባላትና ለቋሚ ሲቪል ሰራተኞቹ በሃዋሳ ያስገነባቸውን 232 የጋራ መኖሪያ ቤቶች በእጣ የማስተላለፍ መርሃ ግብር አከናውኗል፡፡ በወቅቱም ሚኒስትሯ አይሻ መሃመድ (ኢ/ር) እንደገለጹት፤ የለውጡ መንግስት ባከናወነው የሪፎርም ስራ በፈተናዎች የማይበገር ብቃቱ የተረጋገጠ የሀገር መከላከያ ሰራዊት መገንባት ተችሏል። የለውጡ መንግስት እውን ባደረገው የሪፎርም ስራ መሰረት በወጣው የመከላከያ ሰራዊት አዋጅ የሰራዊቱን ክብር የሚመጥኑ ጥቅማ ጥቅሞች በሚገባ እንዲከበሩ ተደርጓል ብለዋል። በዚህም ለሀገር ሉዓላዊነትና ለህዝብ ሰላም የህይወት መስዋዕትነት ለሚከፍል የመከላከያ ሰራዊት ጥቅም መከበር የሚደረግ ድጋፍ ውለታ ሳይሆን የክብር ግዴታ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽን የተገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች መንግስትና ህዝብ ለሰራዊቱ ያላቸውን ምስጋናና ፍቅር በተግባር ያሳዩበትና ሀገራዊ ህሊና የወለዳቸው የእውቅና ውጤቶች ናቸው ሲሉ ገልጸዋል፡፡ ፕሮጀክቱ በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ የተደረገው የጋራ ርብርብ የኢትዮጵያውያንን የመደጋገፍና የአብሮነት ጥበብ ያሳየ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሯ የመኖሪያ ቤቶቹ ፋውንዴሽኑ በራሱ ባለሙያዎች የገነባው መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ የጋራ መኖሪያ ቤቶቹ ግንባታ ሰራዊቱ ራሱንና ቤተሰቡን በተረጋጋ መንገድ በማኖር ሀገራዊ ግዳጁን በተገቢው እንዲወጣ የሚያደርግና ለሃዋሳ ከተማ ተጨማሪ ውበትና የልማት ውጤት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የሲዳማ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ሃላፊ አቶ በየነ በራሳ በበኩላቸው የመከላከያ ሰራዊት ለሀገር ሉአላዊነት፣ ክብርና ለህዝብ ሰላም በታማኝነት የሚያገለግልና የህይወት መስዋዕትነት የሚከፍል ነው ብለዋል፡፡ በዛሬው እለት የተመረቁ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ከ820 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የመከላከያ ሚኒስቴር ፋውንዴሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ሜጀር ጄኔራል ደረጀ መገርሳ ናቸው፡፡ የጋራ መኖሪያ ቤቶቹ በአነስተኛ ወጪ በራስ አቅም የተገነቡ መሆናቸውን ጠቅሰው ሰራዊቱ ለሀገርና ለህዝብ ለሚከፍለው መስዋእትነት እውቅና የሚሰጡ በመሆናቸው ተግባሩ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ ከመኖሪያ ቤት ባለእድለኞች መካከል ሌተናል ኮሎኔል ታመነች ተሰማ እና ሌተናል ኮሎኔል አክሊሉ አሻንጎ የቤት ባለቤት በመሆናቸው ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸው፤ መንግስት ሰራዊቱን የቤት ባለቤት ለማድረግ የጀመረው ስራ የሚደነቅ ነው ብለዋል፡፡ ይህም ሰራዊቱ ራሱንና ቤተሰቡን በተረጋጋ ሁኔታ እንዲመራና ግዳጁን በተገቢው እንዲወጣ የሚያስችልና ተስፋን የሚሰጥ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በመርሃ ግብሩ ላይ የመከላከያ ሚኒስቴር ከፍተኛ አመራሮች፣ የተለያየ ማዕረግ ያላቸው የሰራዊት አባላትና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።
መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭትን በማሳለጥ በኩል ከፍተኛ ለውጥ አስገኝቷል
May 23, 2026 192
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭትን በማሳለጥ በኩል ከፍተኛ ለውጥ ማስገኘቱን ኢዜአ ያነጋገራቸው አሽከርካሪዎች እና የነዳጅ ማደያዎች ገለጹ፡፡ በመካከለኛው ምስራቅ ተከስቶ የነበረውን ችግር ተከትሎ በዓለም አቀፍ ደረጃ በነዳጅ ምርት አቅርቦት ላይ የተፈጠረው ክፍተት፣ በሀገር ውስጥም የነዳጅ አቅርቦት መስተጓጎል አስከትሎ የነበረ ቢሆንም፤ መንግሥት አቅርቦቱ ከጦርነቱ በፊት ወደነበረበት ደረጃ እንዲመለስ አድርጓል። መንግሥት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ የነበረውን ዓለም አቀፍ ተጽዕኖ ተቋቁሞ ለማለፍ ያስቻለ ሲሆን፣ አሁን ላይ በተለያዩ ከተሞች የተረጋጋ፣ ቀልጣፋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት እንዲኖር አስችሏል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ሚያዝያ 21 ቀን 2018 ዓ.ም በወቅታዊ የዓለም የነዳጅ ሁኔታን በማስመልከት በሰጡት ማብራሪያ፣ የናፍጣ ነዳጅ አቅርቦት ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት ወደነበረበት እንዲመለስ መደረጉን መጥቀሳቸው ይታወቃል፡፡ ኢዜአ በመዲናዋ ያነጋገራቸው አሽከርካሪዎችና የነዳጅ ማደያ ባለቤቶች፤ መንግሥት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደውን የማሻሻያ እርምጃ ተከትሎ በአቅርቦቱና በስርጭቱ ላይ ከፍተኛ አዎንታዊ ለውጥ መታየቱን ገልጸዋል። አስተያየት ከሰጡ አሽከርካሪዎች መካከል አባይነህ ይሁኔ፤ ቀደም ሲል ከዓለም አቀፉ የነዳጅ እጥረት ጋር ተያይዞ በነበረው መስተጓጎል በእለት ተእለት እንቅስቃሴያቸው ላይ ከፍተኛ ችግር ገጥሟቸው እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ላይ ግን የነበረው ችግር ሙሉ በሙሉ ተፈትቶ ሁኔታው ወደ ቀድሞው በመመለሱ፣ በሁሉም ማደያዎች የሚፈልጉትን ያህል ነዳጅ ያለምንም እንግልት እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ሌላኛው አሽከርካሪ ከድር ሁሴን በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል ነዳጅ ለማግኘት እስከ አንድ ሳምንት ይወስድባቸው የነበረው አስቸጋሪ ሁኔታ በአሁኑ ወቅት ሙሉ በሙሉ መፈታቱንና ያለምንም እንግልት ነዳጅ እያገኙ ማኅበረሰቡን በሚገባ እያገለገሉ መሆናቸውን አስረድተዋል። በተመሳሳይ አሽከርካሪ ተፈሪ ዓለሙ እና ረታ ጂቢቲ እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል ተከስቶ የነበረው የነዳጅ እጥረትና የረጅም ሰዓት ወረፋ በመንግሥት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት በመቀረፉ፣ በአሁኑ ወቅት ያለምንም መስተጓጎል እየተስተናገዱ ይገኛሉ። በነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ላይ የነበረው ችግር በመወገዱ በአሁኑ ወቅት የተረጋጋ ሁኔታ መፈጠሩንና መደበኛ ሥራቸውን በተሻለና ይበልጥ ውጤታማ በሆነ መልኩ እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። የነዳጅ ማደያ ሱፐርቫይዘሮች በበኩላቸው ቀደም ሲል በዓለም አቀፍ የነዳጅ ቀውስ ምክንያት ይፈጠር የነበረው የአቅርቦት ችግር በመቀረፉ ደንበኞቻቸውን ያለምንም እንግልት እያስተናገዱ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በአቅርቦትና በስርጭት ላይ ችግር አለመኖሩን ጠቁመው ለማኅበረሰቡ ጥሩ አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በቡልጋሪያ አካባቢ የቶታል ማደያ ሱፐርቫይዘር ሰለሞን ገብረሕይወት እና በአሮጌው ቄራ አካባቢ ቶታል ማደያ ሱፐርቫይዘር ይርጋ ኪዳነ ማርያም ቀደም ሲል በነበረው እጥረት ምክንያት ተሽከርካሪዎች ነዳጅ ለማግኘት እስከ አምስት ቀናት የሚደርስ ረጅም ሰልፍ ይጠብቁ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ላይ ችግሩ ሙሉ በሙሉ መቀረፉን አረጋግጠዋል። በተመሳሳይ የሜክሲኮ አካባቢ የካምፖ አስመራ ነዳጅ ማደያ ሱፐርቫይዘር ጥበቡ በቀለ በበኩላቸው፤ መንግሥት ዓለም አቀፉን የነዳጅ አቅርቦት ቀውስ ለማስተካከል የወሰደውን ቁርጠኛ እርምጃና የመጣውን ፈጣን አዎንታዊ ለውጥ አድንቀዋል። በአሁኑ ወቅት ነዳጅ ለማደያቸው በአግባቡና በወቅቱ እየቀረበ መሆኑን ገልጸው እያገኙት ያለውን ምርትም ለተጠቃሚ አሽከርካሪዎች እያቀረቡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።
የአካባቢ ጸጋዎችን መሰረት ያደረጉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገቡ ነው
May 23, 2026 142
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በየአካባቢው የሚገኙ የፈጠራና የተፈጥሮ ጸጋዎችን በመለየትና የሥራ ዕድሎችን በማስፋፋት ተጨባጭ ውጤቶች እየተገኙ መሆኑን የተለያዩ ክልሎች የሥራና ክህሎት ቢሮ የሥራ ኃላፊዎች ገለጹ። በኢትዮጵያ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ፣ የግል ዘርፉን ለማበረታታትና የሥራ አጥነት ቁጥርን ለመቀነስ በርካታ መዋቅራዊና ሕጋዊ ሪፎርሞች ተከናውነዋል። ለአብነትም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ማስፋፋት፣ ለሥራ ዕድል ቅድሚያ የሚሰጥ ስትራቴጂ ትግበራ፣ ተቋማዊ ሪፎርም እንዲሁም የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪትን ማመቻቸት በዋናነት የሚጠቀሱ ተግባራት ናቸው። የተለያዩ ክልሎች የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአካባቢ ጸጋዎችን በጥናት በመለየት የሥራ ዕድልን ለማስፋፋት የተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶችን አስገኝተዋል። የአካባቢውን ጸጋ ተጠቅመው ዜጎች በማኅበረሰብና በቤተሰብ የንግድ ሥራዎች ላይ እንዲሰማሩ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን አመልክተው፤ የሥልጠና፣ የብድር እና የሌሎች ተያያዥ ድጋፎችን በማድረግ የዜጎች ውጤታማነት ይበልጥ እየጎለበተ መምጣቱን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት አማካኝነት የሥራ ፈላጊዎች ምዝገባና የሥራ ዕድል ፈጠራ መረጃዎችን በዘመናዊ መልኩ በማደራጀት፣ ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተደራሽ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ኃላፊዎቹ ጠቁመዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ምክትል ቢሮ ኃላፊ ተመስገን ኃይሌ፤ በክልሉ የሀገር ውስጥ የሥራ ዕድሎችን ለማሳደግ የአካባቢ ጸጋዎችን በመለየት ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ለዜጎች የክህሎት፣ የአቅም ግንባታና ሌሎች ድጋፎችን በማመቻቸት እና የሥራ ዕድል ፈጠራው ክህሎት መር በማድረግ እስካሁን ለ280 ሺህ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቁመዋል፡፡ በሲዳማ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ከፍያለው ከበደ በበኩላቸው፤ በክልሉ በስፋት የሚገኙ ምርቶችን በመለየት የማኅበረሰብና የቤተሰብ የንግድ ሥራዎችን ከሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ጋር በማስተሳሰር ውጤታማ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ የሥራ ስምሪትና ገበያ ልማት ዘርፍ ኃላፊ ዘውዱ ሳሙኤል፤ በክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት ያደረገው በአካባቢ ጸጋዎችና አቅሞች ላይ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ዜጎች ተደራጅተው በአካባቢው በሚገኙ ጸጋዎች ላይ እሴት በመጨመር በስፋት እንዲያመርቱና ወደ ገበያ እንዲያስገቡ በማድረግ በኩል ስኬታማ ሥራዎች መከናወናቸውን አስገንዝበዋል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን በመጪው ክረምት በ39 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ ይተከላል
May 23, 2026 130
ነቀምቴ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን በመጪው ክረምት በ39 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ እንደሚተከል የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በጽህፈት ቤቱ የቡና ምርት ቡድን መሪ አሰፋ መኮንን እንደገለጹት፤ በዞኑ የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተተገበረ ባለው ኢኒሼቲቭ የአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት እያደገ መጥቷል። በተያዘው ዓመት ክረምትም በ39 ሺህ 983 ሄክታር መሬት ላይ በአጭር ጊዜ ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ 279 ሺህ 632 የቡና ችግኝ ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ብለዋል። ችግኞቹም በመንግስት፣ በማህበራትና በአርሶ አደሮች የችግኝ ጣቢያዎች እንዲባዙ ተደርጎ በአሁኑ ወቅት ለተከላ ዝግጁ መደረጉን ገልጸዋል። ከችግኝ ዝግጅትና ተከላ ጋር ተያይዘው የሚታዩ ክፍተቶችን ለማረምም የባለሙያዎች የአቅም ግንባታና የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ እየተሰጠ ነው። የቡና ምርትና ምርታማነትን በተሻለ ደረጃ ለማሳደግ ያረጀና ምርት የማይሰጥ የቡና ተክል ጉንደላ ሲከናወን መቆየቱን ጠቅሰው የተጎነደሉ ተክሎች በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ መልሰው ምርት የሚሰጡ መሆኑንም ተናግረዋል። በዞኑ የጉቶ ጊዳ ወረዳ አርሶ አደር ሹምዬ ባይሳ እና አርሶ አደር ገመቹ ደረጄ በሰጡት አስተያየት፤ ቀደም ሲል በባህላዊ መንገድ ያመርቱ ስለነበር በሚፈለገው ልክ መጠቀም እንዳልቻሉ ገልጸዋል።
በአማራ ክልል የከተማ ነዋሪዎችን የቤት ባለቤት ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
May 23, 2026 140
ጎንደር፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የከተማ ነዋሪዎችን የቤት ባለቤት ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) ገለጹ። የጎንደር ከተማ አስተዳደር በ550 የመኖሪያ ቤት ሕብረት ሥራ ማኅበራት ለተደራጁ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች የቤት መስሪያ ቦታ፣ የሳይትና የብሎክ ርክክብ መርሃ ግብር አካሂዷል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የቢሮው ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ የክልሉ መንግሥት የቤት ልማት ፖሊሲና ስትራቴጂውን ወደ ተግባር በማውረድ፣ በመካከለኛና በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የኅብረተሰብ ክፍሎችን በተለያዩ አመራጮች የቤት ባለቤት ለማድረግ እየሠራ ነው። መንግሥት የሕዝቡን አቅም በማስተባበርና ዘመናዊ አሠራር በመዘርጋት የቤት አቅርቦት ችግርን ለመፍታት የተቀናጀ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። መሬት ውድና ውስን ሀብት በመሆኑ ለጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ትኩረት በመስጠት፣ ለኑሮ ምቹና ውብ የሆኑ ዘመናዊ ከተሞችን ለማስፋፋት የቤት ልማት ፖሊሲውን መሠረት ያደረጉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። የጎንደር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው በበኩላቸው፤ በማኅበራት የተደራጁ ነዋሪዎች ፈጥነው ወደ ግንባታ መግባት እንዲችሉ ከተማ አስተዳደሩ መሠረተ ልማቶችን በፍጥነት እንደሚያሟላ ገልጸዋል። ማኅበራቱ በገቡት ውል መሠረት ግንባታቸውን በፍጥነት መጀመር እንዳለባቸው ያሳሰቡት ምክትል ከንቲባው፤ መሬት አጥረው ለረጅም ዓመታት በሚያቆዩ ማኅበራት ላይ ጥብቅ ክትትል በማድረግ ከተማ አስተዳደሩ ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ አስታውቀዋል። የከተማ አስተዳደሩ የመሬት መምሪያ ኃላፊ አቶ ታዛዙ በጽሐ፤ በዛሬው ዕለት የቅየሳና የብሎክ ሥራ ተሠርቶላቸው የመኖሪያ ቤት ግንባታ ቦታ ተጠቃሚ የሆኑት ከ13 ሺህ በላይ አባላትን ያቀፉ 550 የቤት ሥራ ማኅበራት መሆናቸውን አስታውቀዋል። ለእያንዳንዱ የማኅበር አባል 150 ካሬ ሜትር የግንባታ ቦታ መዘጋጀቱን የጠቆሙት ኃላፊው፤ ከተጠቃሚዎቹ መካከል የመንግሥት ሠራተኞች፣ መምህራንና የጤና ባለሙያዎች፣ ሴቶች፣ ወጣቶችና አካል ጉዳተኞች፣ በክብር የተመለሱ የሠራዊት አባላት፣ እንዲሁም ከስደት ተመላሾች እንደሚገኙበት አስረድተዋል። የቤት መስሪያ ቦታ ተጠቃሚ ከሆኑት ነዋሪዎች መካከል አቶ ታደለ በላይ በሰጠው አስተያየት፤ ለረጅም ዓመታት በግለሰብ ቤት ኪራይ አስቸጋሪ ሕይወት ሲመራ መቆየቱን ገልጾ፣ አሁን ቦታውን በማግኘቱ ፈጥኖ በመገንባት የቤት ባለቤት ለመሆን መወሰናቸውን ተናግረዋል። ወጣት አማኑኤል ምሕረቱ በበኩሉ፤ የቤት መስሪያ ቦታ ዕድለኛ በመሆኑ የተሰማውን ከፍተኛ ደስታ ገልጿል። በዚሁ የርክክብ ሥነ-ሥርዓት ላይ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በቤት ሥራ ማኅበራት የተደራጁ በርካታ የከተማዋ ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
የግራንዴር ሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ የሚያደርግ ነው
May 23, 2026 370
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ የግራንዴር ሴራሚክ ማምረቻ መከፈት የኢትዮጵያን የውጭ ምርት ጥገኝነት ከመቀነስ ባሻገር ኢትዮጵያን በዘርፉ በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ የሚያደርግ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በሞጆ ከተማ የተገነባውን የግራንዴር ሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካን መርቀዋል። በሞጆ ከተማ በግራንዴር ሴራሚክ ማኑፋክቸሪንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር የተገነባው የሴራሚክና የፖርሲሌን ንጣፎች ማምረቻ ፋብሪካ፣ ከዕቅድና መሬት ዝግጅት እስከ ሙሉ ሥራ ማስጀመር የወሰደው ጊዜ ዘጠኝ ወራት ብቻ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ገልጿል። መሰረተ ልማቱ በ300,000 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያረፈው ይህ ፋብሪካ፣ የዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀና ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ መዋዕለ-ነዋይ የወጣበት ሲሆን፤ በኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር ጉዞ ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ ያመላከተ ክንውን መሆኑ ተመላክቷል። በአሁኑ ወቅት 60x60 የሴራሚክ ንጣፎችን በስፋት ማምረት የጀመረው ይህ ፋብሪካ፤ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ውስጥ የምርት ዓይነቶቹን በማስፋት የ80x80bg፣ 60x120፣ 70x140 እና 80x160 መጠን ያላቸውን የንጣፍ ዓይነቶች እንዲሁም የአውሮፓን የጥራት ደረጃ ያሟሉ የፖርሲሌን ምርቶችን ማቅረብ እንደሚጀምር ይጠበቃል። ለፋብሪካው ምርት የሚያስፈልጉት ጥሬ ዕቃዎች 80 በመቶ የሚሆነው ከፋብሪካው በ100 ኪሎ ሜትር ክበብ ውስጥ የሚገኙ በመሆኑ፣ ሙሉ በሙሉ የተቀናጀና ከአካባቢው ማኅበረሰብ ጋር የተሳሰረ የአቅርቦት ሰንሰለት መፍጠር ተችሏል። ኢትዮጵያ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት ባሳለፍናቸው ዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ ከ4.85 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማዳን በቻለችበት በዚህ ወቅት፤ የግራንዴር ሴራሚክ መከፈት የውጭ ምርት ጥገኝነትን የሚቀንስ ብቻ ሳይሆን፣ ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ተወዳዳሪ እንድትሆን የሚያስችላትም ጭምር መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።
የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭት መሻሻል በሀዋሳ ከተማ የትራንስፖርትና ንግድ እንቅስቃሴን ይበልጥ አሳልጧል
May 23, 2026 129
ሀዋሳ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ በሀዋሳ ከተማ የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭት በመሻሻሉ በትራንስፖርትና በንግድ እንቅስቃሴ ላይ ተፈጥሮ የነበረው ጫና መቀረፉን የከተማዋ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ አስታወቀ፡፡ መንግስት በመካከለኛው ምስራቅ በተፈጠረው ችግር ምክንያት ያጋጠመውን የነዳጅ አቅርቦት ችግር መቋቋም ያስቻሉ የመፍትሄ እርምጃዎችን መተግበሩ ይታወሳል፡፡ በሀዋሳ ከተማም መንግስት የወሰዳቸውን የመፍትሄ እርምጃዎች ተከትሎ የአቅርቦት ሁኔታው ወደነበረበት ተመልሷል። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አገና ኔቶ እንደገለጹት፤ የነዳጅ አቅርቦት መሻሻሉ በከተማዋ የትራንስፖርትና ንግድ እንቅስቃሴ የበለጠ እንዲሳለጥ አስችሏል። በከተማው በመንግስት በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ነዳጅ በቁጠባ ጥቅም ላይ እንዲውል ሲደረግ መቆየቱንም አስታውሰዋል። በተለይም ለሕዝብ ትራንስፖርት፣ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች እንዲሁም ሸቀጣሸቀጦችን ለሚያጓጉዙ የጭነት ተሽከርካሪዎች ቅድሚያ በመስጠት የማዳረስ ሥራ ሲሠራ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ መንግስት ችግሩን ለመቅረፍ በወሰደው ቁርጠኛ አቋም አቅርቦቱ ወደ ነበረበት መመለሱንና በዚህም በትራንስፖርትና በንግድ እንቅስቃሴ ላይ ተጨባጭ ለውጥ መታየቱን ተናግረዋል። መምሪያውም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት የነዳጅ ስርጭቱ በአግባቡና በፍትሐዊነት እንዲዳረስ የክትትል ሥራውን አጠናክሮ መቀጠሉን ጠቁመዋል፡፡ ማደያዎች እና አሽከርካሪዎች በበኩላቸው ቀደም ሲል በነዳጅ አቅርቦት እጥረት ምክንያት በማደያዎች አካባቢ ረጅም ሰዓት ይሰለፉ እንደነበር አስታውሰው፣ አሁን ላይ ግን አቅርቦቱ ወደ ቀድሞ ሁኔታው መመለሱን ተናግረዋል፡፡ የሕዝብ ማመላለሻ ትራንስፖርት አሽከርካሪው ታረቀኝ ኢዩኤል ከሀዋሳ ወደ ተለያዩ ከተሞች የትራንስፖርት አገልግሎት እንደሚሰጡ ገልጸዋል። የነዳጅ አቅርቦቱ ውስን በሆነበት ወቅት እኛም ሆንን ማኅበረሰቡ ለከፍተኛ ችግር ተዳርገን ነበር፤ ነዳጅ በሳምንት አንድ ወይም ሁለት ጊዜ ብቻ የምናገኝበት አጋጣሚ ነበር ብለዋል። አሁን ላይ ግን ያለ ምንም እንግልት በቀላሉ ነዳጅ እያገኘን ማኅበረሰቡን በሚገባ ማገልገል ችለናል ሲሉ ገልጸዋል። ሌላው በጭነት ትራንስፖርት ሰጪ ተሽከርካሪ ላይ ረዳት ሆነው እየሠሩ የሚገኙት ሲሳይ ጌጣ፤ በአብዛኛው እህልና ሸቀጣሸቀጦችን የማጓጓዝ ሥራ እንደሚሠሩ ተናግረዋል። አሁን የነዳጅ አቅርቦቱ በመሻሻሉ መደበኛ ሥራቸውን በተሻለ ሁኔታ ማከናወን መቻላቸውን አስረድተዋል። በሀዋሳ ከተማ የታፍ ነዳጅ ማደያ ሥራ አስኪያጅ ያሬድ ካሱ፤ ነዳጅ በአግባቡ እየቀረበ እያገኘን ነው፤ እኛም ለተጠቃሚዎች ፍትሐዊ በሆነ መንገድ እያደረስን ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የግራንዴር ሴራሚክ ፋብሪካን መረቁ
May 23, 2026 209
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የግራንዴር ሴራሚክ ፋብሪካን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሴራሚክ ፋብሪካው የአምራች ኢንዱስትሪ ልማት ጉዞ አካል እና የ“ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ እመርታ ትልቅ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ቁልፍ ሀገራዊ ፋይዳ ያላቸውን መሰል ፋብሪካዎች ግንባታ፣ ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንቶችን በመሳብ በመላ ሀገሪቱ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በተግባር ያረጋገጠ ነው ብለዋል። ፋብሪካው የዓለም ዓቀፍ ጥራትና ተወዳዳሪነት መስፈርቶችን የሚያሟሉ የሴራሚክ ምርቶችን የሚያቀርብ ሲሆን፣ ለምርቱ የሚያስፈልጉትን ጥሬ ዕቃዎች ከ80 በመቶ በላይ ከሀገር ውስጥ ዐቅም እንደሚያገኝ ጠቁመዋል። ይህ ስኬት ኢትዮጵያ የራሷን የተፈጥሮ ሀብትና እምቅ ጸጋ የመጠቀም ብቃቷን ከመገንባቱ ባሻገር፣ ከውጭ ገቢ ምርቶች ላይ ያለንን ጥገኝነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚቀንሰውም ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት።
መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭቱ የተሳለጠ እንዲሆን አስችሏል
May 23, 2026 138
አዳማ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የወሰደው እርምጃ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦት እና ስርጭቱ የተሳለጠ እንዲሆን ማስቻሉን የአዳማ ከተማ አስተዳደር ንግድ ጽህፈት ቤት ገለጸ። በመካከለኛው ምስራቅ ተከስቶ የነበረውን ጦርነት ተከትሎ፣ በተለይም በነዳጅ ምርት አቅርቦት ላይ ዓለምአቀፍ ችግር አስከትሎ እንደነበር ይታወሳል። ይህ ችግር በኢትዮጵያ የነዳጅ አቅርቦት ላይ መስተጓጎል ፈጥሮ የነበረ ቢሆንም መንግሥት በአቅርቦትና ስርጭት ላይ አዲስ አሰራር ተግባራዊ በማድረግ ችግሩን ለማቃለል ጥረት አድርጓል። በዚህም የነበረውን ዓለም አቀፍ ችግር በመቋቋም ማለፍ የተቻለ ሲሆን፣ አሁን ላይ በተለያዩ ከተሞች የተረጋጋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት መኖሩን ለማወቅ ተችሏል። በኦሮሚያ ክልል አዳማ ከተማ አሁናዊ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱ ምን እንደሚመስል ኢዜአ የሚመለከታቸውን አካላት፣ የነዳጅ ማደያዎችንና አሽከርካሪዎችን አነጋግሯል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ንግድ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ጢሎ ዱግዳ፤ በነዳጅ አቅርቦት ላይ አጋጥሞ የነበረውን ችግር ለመቋቋም በከተማ አስተዳደሩ የነዳጅ ስርጭት ግብረ ኃይል ተቋቁሞ፣ የነዳጅ ስርጭቱ ፍትሃዊ እና ተደራሽ እንዲሆን መስራቱን አንስተዋል። በመሆኑም አሁን ላይ በከተማዋ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ችግር የሌለ በመሆኑ ጥሩ አገልግሎት እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል። በከተማዋ በሚገኙ 19ኝ ማደያዎች በቂ የነዳጅ አቅርቦት መኖሩን ገልጸው፣ በዚህም ተገልጋዮች ካለምንም እንግልት እየተጠቀሙ መሆኑንና የእንቅስቃሴ ችግር አለመኖሩን አንስተዋል። በከተማዋ ቀደም ሲል ህገወጥ የነዳጅ ዝውውርን ለመግታት በተደረገ ቁጥጥር 6ሺህ ሊትር ናፍጣና 6ሺህ ሊትር ቤንዚን መያዙን አስታውሰው፣ ህግ የማስከበር ስራ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል ብለዋል። በከተማዋ ከሚገኙ ነዳጅ ማደያዎች መካከል የኖክ ነዳጅ ማደያ ስራ አስኪያጅ ግዛው አበበ እና የአፍሪካ ቁጥር 1 ነዳጅ ማደያ ስራ አስኪያጅ ኮሚኒስት ወንድሙ፤ ቀደም ሲል በነዳጅ አቅርቦት ላይ የነበረው ችግር በመፈታቱ ደንበኞች በአግባቡ እየተስተናገዱ መሆኑን ገልጸዋል። ከአሽከርካሪዎች መካከል ጌቱ ተስፋዬ እና አሸናፊ አለሙ፤ በነዳጅ አቅርቦትና ስርጭት ላይ የነበረበው ችግር በመፈታቱ አሁን ላይ የተረጋጋ ሁኔታ እንዳለ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተግዳሮቶችን በጽናት በማለፍ በስኬት ጎዳና ላይ ይገኛል
May 22, 2026 649
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚያጋጥሙትን ተግዳሮቶች በጽናት በማለፍ በስኬት ጎዳና ላይ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ እና የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ80ኛ ዓመት ክብረ በዓል ማጠቃለያ መርሐ-ግብር አካሂዷል። በማጠቃለያው መርሐ-ግብር ላይ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ እንግዶች ታድመዋል። የቦርድ ሰብሳቢው ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ በመድረኩ ባደረጉት ንግግር፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሀገሪቱን ለዓለም የሚያስተዋውቅ ብርቅዬ ተቋም መሆኑን ገልጸዋል። አየር መንገዱ በሚሰጠው የላቀና ዘመናዊ አገልግሎት ምክንያት፣ ከበርካታ ዓለም አቀፍ ተቋማት በየዘመኑ ከፍተኛ እውቅና እየተሰጠው እንደሚገኝም ጠቁመዋል። አየር መንገዱ በየጊዜው የሚያጋጥሙትን የተለያዩ ተግዳሮቶች በጽናት በማለፍ ሁልጊዜም በስኬት ጎዳና ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ተቋሙ ከአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድነት ባለፈ፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪነቱን ይበልጥ ለማሳደግ ስትራቴጂ ቀርጾ በስፋት እየሠራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት መንግሥት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት በተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ ሥራዎች አየር መንገዱ ስኬቶቹን አጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም ተቋሙ ለበለጠና ለላቀ ስኬት በከፍተኛ ቁርጠኝነት እንደሚሠራ አረጋግጠዋል።