ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በክልሉ በበልግ አዝመራ በሆርቲካልቸር እና በዋና ዋና ሰብሎች ከ575 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ ለምቷል
May 15, 2026 246
ቦንጋ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በተያዘው የበልግ አዝመራ በሆርቲካልቸር እና በዋና ዋና ሰብሎች ከ575 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ መልማቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ኃላፊ ማስረሻ በላቸው የበልግ እርሻ አፈፃፀምን በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል። በዚህም በዘንድሮ የበልግ አዝመራ የዜሮ ግብ አቅጣጫን በመከተል ከዚህ ቀደም የማይታረሱ ማሳዎች ጭምር እንዲታረሱ በተደረገ ርብርብ 575 ሺህ 160 ሄክታር ማሳ በሆርቲካልቸር እና በዋና ዋና ሰብሎች መልማቱን ተናግረዋል። ዘንድሮ በበልግ የለማው መሬት ከአምና በ50 ሺህ ሄክታር ጭማሪ እንዳለው ገልጸው፤ በዋና ዋና ሰብሎች ብቻ ከለመው መሬት 16 ሺህ ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ግብ መተጣሉን አንስተዋል። በእስካሁኑ ሂደት 422 ሺህ 87 ሄክታር ማሳ በዘር መሸፈኑን ጠቁመው፤ ከዚህም ውስጥ 129 ሺህ 200 ሄክታሩ በክላስተር የለማ ነው ብለዋል። የሚታረስ ማሳን መጠን ከማሳደግ ባለፈ 46 ሺህ 200 ሄክታር በትራክተር መታረሱን ያነሱት አቶ ማስረሻ፣ ይህም አርሶ አደሩ የሜካናይዜሽን እርሻን ለመጠቀም ፍላጎቱ እያደገ መምጣቱን ያሳያል ብለዋል። በክልሉ ለኤክስፖርት ምርቶች በተሰጠ ልዩ ትኩረትም ከ42 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት በቅባት እህሎች፣ በማሾ፣ በሰሊጥ፣ በቦሎቂና በሌሎች ሰብሎች መሸፈኑን ጠቁመዋል። ፍራፍሬ ሌላው ትኩረት የተሰጠው የሆርቲካልቸር ሰብል መሆኑን ገልጸው፤ ችግኞችን አዘጋጅቶ ከመትከል ባለፈ ምርታማነትን ለማሳደግም ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል። እንደ ሀላፊው ገለጻ፣ በበልግ ወቅት 50 ነጥብ 8 ሚሊዮን በላይ የፍራፍሬ ችግኞችን በማዘጋጀት ለመትከል ታቅዶ እስካሁን 50 ነጥብ 6 ሚሊዮን ችግኞች ተዘጋጅተዋል። እስካሁንም 23 ነጥብ 6 ሚሊዮን ችግኞች መተከላቸውን ጠቁመው፣ በፍራፍሬ ልማቱ ከነባር ማሳ 19 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል የሚሆን ምርት ተሰብስቧል ብለዋል። የእንሰት ልማትን ለማስፋት በተሰጠው ልዩ ትኩረት 95 ነጥብ 6 ሚሊዮን የእንሰት ችግኞች መተከላቸውን ተናግረዋል። የግብርና ግብአት አጠቃቀምን ለማሳደግ በተሰጠ ትኩረትም መሻሻል እንዳለ ገልጸው፣ በበልግ ወቅት 159 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር እንዲሁም 86 ሺህ 205 ኩንታል ዩሪያና ዳፕ የአፈር ማዳበሪያ ጥቅም ላይ ውሏል ብለዋል። ከበልግ የእርሻ እንቅስቃሴ በአጠቃላይ ከ70 ሚሊዮን ኩንታል በለይ ምርት ለመሰብሰብ ግብ የተያዘ ሲሆን፣ ይህን ለማሳካት የአረም ቁጥጥርና የተባይ አሰሳ ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑንም ተናግረዋል።
የአዲስ አበባ አስደናቂ የልማት ስኬት የመደመር ዕሳቤ ለትውልድ የሚሻገር ጥበብ የተገለጠባትን ከተማ ፈጥሯል
May 15, 2026 237
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ አስደናቂ የልማት ስኬት የመደመር ዕሳቤ ለትውልድ የሚሻገር ጥበብ የተገለጠባትን ከተማ መፍጠሩን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ እና የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የአዲስ አበባን የለውጥ ጉዞ በተመለከተ በዓለም አቀፍ ምሁራንና ተመራማሪዎች የተጻፈውን "THE REMAKING OF ADDIS ABABA" የተሰኘውን መፅሐፍ መርቀዋል።   በዓለም አቀፍ ምሁራንና ተመራማሪዎች የተሰነደው መፅሐፍ አዲስ አበባ በአጭር ጊዜ ያስመዘገበችውን አስደናቂ ዕድገት ለታሪክ፣ ለመልካም ተሞክሮ፣ ለጥናትና ምርምር እንዲያገለግል የተሰናዳ ነው። በዚሁ ጊዜ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ በሀገራዊ ለውጡ ስምንት ዓመታት ውስጥ በመዲናዋ የመጣው አስደናቂ ለውጥ የከተማዋን የዕድገት ህልም ወደ ተግባር የለወጠ ነው ብለዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀገር በቀል የመደመር ፍልስፍናም አዲስ አበባን በአጭር ጊዜ ውስጥ ውበትና ፀዳል ያጎናፀፉ የልማት ስኬቶች ባለቤት ማድረጉን ገልጸዋል። የመደመር ፍልስፍና የተበታተኑ አቅሞችን አሰባስቦ በማስተባበር ስብራትን የሚጠግኑና ጉድለትን የሚሞሉ አዳዲስ ዕሴቶችን ፈጥሮ ለቀጣዩ ትውልድ የሚሻገር ጥበብ የተተረጎመበት ዕሳቤ መሆኑን አስረድተዋል። በዕሳቤው መነሻነት በአዲስ አበባ የተገኙ የልማት ስኬቶችም ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ስብራቶችን የሚጠግን አንፀባራቂ ድል የተገኘባቸው መሆናቸውን ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ስኬታማ የለውጥ ጉዞም የህዝብና መንግስትን መተማመንን በማፅናት ደልድይ የገነቡ መሆናቸውን አብራርተዋል። የልማት ሥራዎቹ ህዝቡ በጉልበቱና በገንዘቡ ያደረገው ድጋፍ የአዲስ አበባን ገፅታ ከመቀየር ባሻገር የአብሮነትና የትብብር መንፈስ የጎለበተበትን ወሳኝ ዕድል እንደፈጠረ አንስተዋል።   በመጽሐፉ የተከተቡ መረጃዎችም የአዲስ አበባን ለውጥ በግልፅ የሚናገሩ፣ የተከፈለውን ዋጋና የወገንን ታሪክ ለመቀየር የተደረገውን ቁርጠኝነት የሚያሳዩ ሕያው ምስክሮች ናቸው ብለዋል። መጽሐፉ የእያንዳንዳቸውን ጥረትና ድካም የሚዘክር በመሆኑ መላው የከተማዋ ነዋሪዎች እንዲያነቡትና ለሌሎች እንዲያጋሩት አሳስበዋል። መጪው ትውልድ ከዚህ ተሞክሮ ተምሮ የተሻለች ሀገርና ከተማ እንዲገነባ መነሻ እንደሚሆን እምነታቸውን ገልፀው አዲስ አበባ ወደፊትም አዲስ ታሪክ መጻፏን እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል።
የአዲስ አበባ ለውጥ በጠራ ራዕይ፣ በበሳል አመራር እና በዜጎች ፅኑ ትጋት የተገኘ ስኬት ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 15, 2026 226
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ) ፦ የአዲስ አበባ ሁሉን አቀፍ ለውጥ በጠራ ራዕይ፣ በበሳል አመራር እና በዜጎች ፅኑ ትጋት የተገኘ ስኬት መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና ሌሎች የመንግሥት የሥራ ሀላፊዎች የአዲስ አበባን የለውጥ ጉዞ በተመለከተ በዓለም አቀፍ ምሁራንና ተመራማሪዎች የተጻፈውን "THE REMAKING OF ADDIS ABABA" የተሰኘውን መፅሐፍ መርቀዋል።   ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚህ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት መጽሐፉ የአዲስ አበባን መልክ መቀየር ብቻ ሳይሆን፤ የአንድን ትውልድ የማይበገር ወኔ፣ የታሪክ ስሪት እና የነገን ተስፋ የሚተርክ ህያው ሰነድ ነው ብለዋል። አዲስ አበባ ማንም ባልጠበቀው ፍጥነት እና ባልገመተው ጥራት ተለውጣለች ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ እንደ ስሟ አበባ መሆን ብቻ ሳይሆን፣ ለአፍሪካ ከተሞች የብልፅግና ተምሳሌት የለውጥ መስታወት መሆኗን ገልጸዋል፡፡ አዲስ አበባን የመቀየር ጉዞ የሀሳብ ብቻ ሳይሆን የትልቅ ራዕይ፣ የጠንካራ አመራር እና የጽናት ውጤት መሆኑን በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡ ከተማዋን የማዘመን ስራ ሲጀመር በርካታ ተግዳሮቶች እና ስር የሰደዱ ዘርፈ ብዙ እንቅፋቶች እንደነበሩ አውስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሰጡት በሳልና አርቆ አሳቢ አመራር፣ በከተማዋ አመራር እና በነዋሪዎቿ የቀን ከሌሊት ትጋት ሩቅ ይመስል የነበረው ራዕይ ዛሬ እውን ሆኗል ብለዋል፡፡   "THE REMAKING OF ADDIS ABABA" መጽሐፍ ይህንን የአመራር ጥበብ፣ የትጋት ፍሬ እና የዜጎችን የልፋት ውጤት ቁልጭ አድርጎ ማሳየቱን ገልጸዋል፡፡ ለውጥ ያለ መስዋዕትነት አይመጣም ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ መጽሐፉ በልማት ሂደት ውስጥ ሌሊትና ቀን የደከሙትን፣ በዝናብና ፀሐይ ሳይበገሩ መዲናዋን ለማሳመር ላባቸውን ያፈሰሱ ዜጎችን ድካምና ፍሬ በታሪክ መዝገብ ላይ አስፍሯል ብለዋል፡፡ የመጽሐፉ ዋና ዓላማ ለቀጣዩ ትውልድ ሰርቶ መለወጥ እንደሚቻል ጠንካራ የስራ ባህልን ማሳየት መሆኑን ጠቅሰው፤ መጽሐፉ ለዛሬና ለነገ ትውልድ የትጋትን ኃይልና የማይቻል ነገር እንደሌለ አስተማሪ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአዲስ አበባ የተከናወነው ሥራ የለውጥ ችቦ ሆኖ ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚሸጋገር ታላቅ ቅርስ መሆኑን በመግለጽ፤ ሌሎችም ምሁራን የኢትዮጵያን ዕምቅ ሀብትና ለውጥ በአካል በመመልከት እንዲጽፉ ጥሪ አቅርበዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት ጥያቄ ተገቢና ህጋዊ ነው - አምባሳደር አሌክሲ ላሜክ
May 15, 2026 286
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018(ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት የምታደርገው ጥረት ፍጹም ህጋዊ መሆኑን በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲ ላሜክ ገለጹ። አምባሳደሩ ይህ ጥያቄ በዓለም ላይ በብዛት ህዝብ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለምትሰለፈው ኢትዮጵያ ተገቢና ምክንያታዊ መሆኑንም ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ተናግረዋል። የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ከአንድ ዓመት ተኩል ገደማ በፊት በኢትዮጵያ ባደረጉት ጉብኝት ወቅት የገለጹትን አቋም ያስታወሱት አምባሳደሩ፤ ጉዳዩ አሁንም ቢሆን መሰረታዊና ህጋዊ ጥያቄ ሆኖ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት መፈለጓ ፍጹም ህጋዊ ነው ያሉት አምባሳደሩ፤ ለዚህም የሀገሪቱን ሰፊ የህዝብ ቁጥርና ያላትን መልክዓ-ምድራዊ አቀማመጥ እንደ ዋነኛ ምክንያት ጠቅሰዋል። በርካታ ታዛቢዎች እንደሚስማሙት፣ የቀይ ባህር ጉዳይ ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ቅርስ፣ ከጥንታዊ ስልጣኔዋ፣ ከሀገረ መንግስት ምስረታዋ፣ ከብሄራዊ ደህንነትና ከረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ግቦች ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያለው ነው። ኢትዮጵያም ይህንን መልክዓ-ምድራዊ፣ ታሪካዊና ኢኮኖሚያዊ አውድ መሰረት በማድረግ፣ በጋራ ተጠቃሚነትና በአጋርነት መርህ ላይ የተመሰረተ የባህር በር ተደራሽነትን ለማረጋገጥ እንዲሁም ለጋራ ልማት የሚረዱ ውይይቶችን ስታካሂድ ቆይታለች። ሀገሪቱ የባህር በር ባለቤትነትን በተመለከተ ያላትን ሉዓላዊ መብት ለማረጋገጥ፣ በትውልዶች መካከል የተሸጋገረውን ይህን ጥያቄ በዲፕሎማሲያዊና በህጋዊ መንገዶች መፍትሄ እንዲያገኙ እየሰራች ትገኛለች። አምባሳደር አሌክሲ ፈረንሳይ የኢትዮጵያን የባህር በር ጥያቄ ለመፍታት የሚደረጉ ገንቢ ጥረቶችን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኗን ጠቁመው፤ በዚህ ረገድ ፈረንሳይ የምታበረክተው ማንኛውም እገዛ ካለ ድጋፍ ለመስጠት ፍላጎቱ አለን ብለዋል። ለዚህም የአውሮፓ ሀገራት ተሞክሮ ለቀጣናው ጠቃሚ ትምህርት ሊሰጥ እንደሚችል የጠቆሙት አምባሳደሩ፤ ጠንካራ ኢኮኖሚ ያላቸው በርካታ የአውሮፓ ወደብ አልባ ሀገራት ከጎረቤቶቻቸው ጋር በመተባበር አስተማማኝ የባህር በር ማግኘት መቻላቸውን ለአብነት አንስተዋል። እንደ አምባሳደሩ ገለጻ፣ እነዚህ ሀገራት ወደብ ካላቸው ጎረቤት ሀገራት ጋር በመተማመን ላይ የተመሰረተ ግንኙነትን መገንባት መቻላቸው ለስኬታቸው ቁልፍ ሚና ተጫውቷል። እንዲህ ዓይነቱን ግንኙነት ለመገንባት ጊዜ ቢወስድም፣ አካሄዱ ግን በጣም ውጤታማና የባህር በር አማራጮችን ለማግኘት ተመራጭ መንገድ መሆኑን አመልክተዋል። አምባሳደሩ አክለውም፣ እንዲህ ዓይነቱ ትብብር ወደብ አልባ ከመሆን የሚመነጩና ሊካዱ የማይችሉ ማነቆዎችን ለመፍታት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ እድገትና ቀጣናዊ ትስስርን ለማጠናከር፣ የባህር በር ለማግኘት የምታደርገውን ዲፕሎማሲያዊ ጥረት አጠናክራ ቀጥላለች።
የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለዓለም አቀፍና ዳያስፖራ ማህበረሰብ የማስገንዝብ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል
May 15, 2026 190
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ፍትሐዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለዓለም አቀፍና ዳያስፖራ ማህበረሰብ የማስገንዝብ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን በዚምባቡዌ፣ ዛምቢያና ሞሪሽየስ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደርና የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) የኢትዮጵያ ቋሚ ተጠሪ ረሽድ መሀመድ ገለጹ። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራና ኮሪደር ልማት ውጤታማ ሥራዎች በዲፕሎማሲ መስክ የሀገርን ስምና ገፅታ እያጎሉ እንደሚገኙም ገልጸዋል። አምባሳደር ረሽድ መሀመድ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ በኢ-ፍትሐዊ በደል ከታሪካዊ፣ መልክዓምድራዊና ሕጋዊ የባሕር በር ባለቤትነቷ እንድትነጠል መደረጉን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያ እያስመዘገበችው ካለው ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና ካላት የህዝብ ቁጥር አንጻር በባለቤትነት የምታስተዳድረው፣ የወጪና ገቢ ንግዷን የሚያሳልጥላት አስተማማኝ የባሕር በር እንደሚያስፈልጋት አንስተዋል። በመልክ-ዓምድራዊ አቀማመጥም ከቀይ ባሕር በቅርብ ርቀት ላይ የምትገኝ እንደመሆኗ ከባሕር በር ባለቤትነት ተነጥላ ልትኖር እንደማይቻላት አስገንዝበዋል። ከሶስት አስርት ዓመታት በፊት የባሕር በር ባለቤት የነበረች መሆኗም የባሕር በር ባለቤትነቷን ሕጋዊና ምክንያታዊነት እንደሚያጎላው አብራርተዋል። በዚህም የኢትዮጵያን ታሪካዊ፣ ሕጋዊ፣ መልክዓ-ምድራዊና ፍትሐዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በተለይም ለዚምባቡዌ፣ ዛምቢያ፣ ሞሪሽየስና ኮሜሳ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ የማስገንዘብ ስራ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ አድናቆትና ዕውቅና እየተቸረው እንደሚገኝ ገልጸዋል። በአረንጓዴ አሻራ የተመዘገበውን ስኬት በአፍሪካ ሀገራት ለማስፋት የዲፕሎማቲክ ግሪን ሌጋሲ ፎረም በመመስረት እየተሰራበት መሆኑን ተናግረዋል። በኤምባሲው አስተባባሪነትም በዚምባቡዌ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር እየተካሄደ እንደሚገኝ አንስተዋል። ኢትዮጵያ ከሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት የበለጠ የሚያጠናክር የዲፕሎማሲ ሥራ እየተሰራ እንደሚገኝም አምባሳደሩ ጨምረው ገልጸዋል። ለአብነትም በቅርቡ የኢትዮጵያና ዚምባቡዌ የጋራ ሚኒስትሮች ኮሚሽን ስብሰባ በማካሄድ የሁለትዮሽ ግንኙነትን ይበልጥ የሚያጠናክሩ ስምምነቶችን ለማድረግ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ በዛምቢያ በክብር ቆንፅላ እንድትወከል የሚያስችሉ ሥራዎችን በማከናወን በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ሥራ ለማስገባት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
በክልሉ የአፈር ማዳበሪያ ከአካባቢው የአፈር ሁኔታ ጋር በማስማማት መቅረብ መጀመሩ በምርት ላይ ውጤት እያስገኘ ነው
May 15, 2026 157
ሰመራ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል የአፈር ማዳበሪያን ከአካባቢው የአፈር ሁኔታ ጋር በማስማማት መቅረብ መጀመሩ በምርት ላይ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ገለፀ። ለዘመናት በከብት እርባታ የሚታወቀው የአፋር ህዝብ፣ ከለውጡ ዓመታት ወዲህ ወደ መስኖና ቋሚ ግብርና በስፋት እየተሸጋገረ ይገኛል። የአፈር ለምነትን ለማሻሻልና የግብርና ስራውን የባህላዊ አሰራር ተጽዕኖ በማውጣት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የአፈር ማዳበሪያ አጠቃቀም በክልሉ እየተለመደ መጥቷል። በክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ የእርሻ ኢንቨስትመንትና ግብአት ዘርፍ ምክትል ኀላፊ አቶ ሃሩን ዓሊ እንደተናገሩት፤ የአፈር ማዳበሪያውን ከአካባቢው የአፈር ሁኔታ ጋር በማስማማት ማቅረብ መጀመሩ ምርትን በማሳደግ ላይ ትልቅ መሻሻል አሳይቷል። በበጀት ዓመቱ 50 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለማስገባት ታቅዶ ወደ ስራ የተገባ ሲሆን በእስካሁኑ እንቅስቃሴ 48 ሺህ 800 ኩንታል ቀርቦ በጋሊኮማና ደንከሊያ ዮኒየኖች አማካኝነት በመሠራጨት ላይ መሆኑም ተመላክቷል። በክልሉ የአፈር ማዳበሪያ አጠቃቀም በይፋ መጀመሩን ተከትሎ፣ በተለያዩ የአዝዕርት፣ የፍራፍሬና የአትክልት ምርቶች ላይ ከፍተኛ የሆነ የምርት ጭማሪ መታየቱን ገልጸዋል። ይህ ስኬትም ባለፉት የለውጥ ዓመታት በዘርፉ የተከናወኑ የለውጥ ስራዎችና የተመዘገቡ መሻሻሎች ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በአፋር ክልል የተከናወኑ የግብርና ስራዎች፣ በረሃማ አካባቢዎችን ማልማት እንደማይቻል ይታመንበት የነበረውን የተዛባ ትርክት የቀየሩና ማንኛውንም ሰብል ማምረት እንደሚቻል በተግባር ያረጋገጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የግብዓት አቅርቦቱ ብቻውን ስኬታማ ሊሆን እንደማይችል የጠቀሱት አቶ ሃሩን፣ ማዳበሪያው በአግባቡና በሳይንሳዊ መንገድ ጥቅም ላይ እንዲውል የእያንዳንዱ አርሶ አደር ማሳ በባለሙያዎች እንዲታገዝ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ይህም አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ከቴክኖሎጂው ተገቢውን ውጤት እንዲያገኝና የምርት ብክነትን ለመቀነስ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አብራርተዋል።
በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮ የምርት ዘመን ከ89 ሺህ ኩንታል በላይ የሻይ ምርት ለገበያ ቀርቧል
May 15, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው የምርት ዘመን በ1 ሺህ 280 ሄክታር መሬት ላይ ከለማው ሻይ ከ89 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለገበያ መቅረቡን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የፍራፍሬ ልማት ዳይሬክተር አቶ ቻላቸው አዱኛ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ የሻይ ልማት ኢንሼቲቭ ተቀርጾ ወደ ሥራ ከተገባ ወዲህ የአርሶ አደሩ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መጥቷል። የክልሉ መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ልዩ ትኩረት፣ የምርት ጥራትና ብዛትን የሚጨምሩ የተሻሻሉ የሻይ ዝርያዎች ለአርሶ አደሩ እንዲቀርቡ ተደርጓል ብለዋል። የሻይ ልማቱ በስፋት እየተከናወነ የሚገኘው የክልሉን ዞኖች መልክዓምድርና ተስማሚ የአየር ንብረት መሰረት አድርጎ መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም በጅማ፣ ኢሉባቦር እና ቡኖ በደሌ ዞኖች ውስጥ መሆኑን ጠቁመዋል። ልማቱን ይበልጥ ለማሳደግ የተሻሻሉ ዝርያዎች የሚባዙባቸው የሻይ ችግኝ ጣቢያዎች በመንግስትና በአርሶ አደሮች ደረጃ ተዘጋጅተው ወደ ሥራ ገብተዋል ብለዋል። ባለፉት 9 ወራት ለገበያ የቀረበው ከ89 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ክልሉ በዘርፉ ያለውን እምቅ አቅም የሚያሳይ መሆኑን አቶ ቻላቸው ገልጸዋል። ባለፉት ሦስት ዓመታት አርሶ አደሮች በዘርፉ ወደ ኢንቨስትመንት እንዲሸጋገሩ በተደረገው ጥረት እስካሁን 10 አርሶ አደሮች ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገር መቻላቸውንም አስረድተዋል። በቀጣይም ዘርፉን ይበልጥ ለማዘመን እና የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሻይ ምርት ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎችን ግንባታ ማፋጠን እና ለምርቱ አስተማማኝ የገበያ ትስስር መፍጠር ትኩረት የተሰጣቸው ተግባራት መሆናቸውንም ገልጸዋል። ይህ የሻይ ልማት እንቅስቃሴ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ፣ በባለሀብቶችና በአርሶ አደሮች መካከል ያለውን ቅንጅት በማጠናከር ረገድ ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ዳይሬክተሩ አክለው ገልጸዋል።
በወራቤ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የከተማዋን ገጽታ በመቀየር ለኑሮና ለቱሪዝም ተመራጭ እያደረጓት ነው
May 15, 2026 122
ወራቤ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦በወራቤ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር፣ የወንዝ ዳርቻና የፓርክ ልማት ሥራዎች የከተማዋን ገጽታ በመቀየር ለኑሮና ለቱሪዝም ተመራጭ እያደረጓት መሆኑ ተገለጸ። መንግስት ለከተሞች ልማት ትኩረት በመስጠት ተግባራዊ ያደረገው የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራ ከተሞችን ምቹ፣ ጽዱና ለኑሮ ተመራጭ እያደረጋቸው ነው። ልማቱ በተቀናጀ መንገድ ተግባራዊ ከሆነባቸው ከተሞች አንዷ ወራቤ ስትሆን፣ ልማቱ የከተማዋን ድምቀት ከማጉላት ባለፈ ተወዳዳሪነቷን እያሳደገው መሆኑም ተገልጿል። የወራቤ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ ሻፊ ሙዜ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በከተማዋ እየተተገበረ ያለው የኮሪደር፣ የወንዝ ዳርቻና የፓርክ ልማት ከተማዋን ጽዱና ለኑሮ ምቹ ከማድረግ ባለፈ ለቱሪዝም ያላትን ተመራጭነት እያሳደገው ነው።   የልማት ሥራው በከተማዋ ያሉ ጸጋዎችን ለይቶ ለልማት ለማዋል ማስቻሉን ጠቁመው፣ ለበርካታ የከተማዋ ነዋሪዎችም የሥራ ዕድል በመፍጠር ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። ልማቱ የመዝናኛ ስፍራ፣ የአደባባይ ኹነቶችን ማስተናገጃ ቦታ፣ የመሰብሰቢያ አዳራሽ፣ ምግብ ቤቶች፣ ሰው ሰራሽ ሐይቅና ሌሎች የኮሪደር ልማቶችን አካቶ እየተከናወነ መሆኑንም ጠቅሰዋል። እንደ ምክትል ከንቲባው ገለጻ በከተማው የኮሪደር ልማትን ጨምሮ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች የህዝብ ተጠቃሚነትን በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት እያመጡ ነው።   የወንዝ ዳርቻ፣ የኮሪደርና የፓርክ ልማት ሥራዎችን በማጎልበት የህዝብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና ከተማዋን የሆቴልና ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል ብለዋል። የከተማዋ ነዋሪ ወጣት አብዲ ዋሴ በበኩሉ፤ በከተማው መንገድን ጨምሮ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ መሰረተ ልማቶች እየተከናወኑ መሆኑን ነው የገለጸው።   የልማት ሥራዎቹ ከተማዋን ምቹ፣ ማራኪና ተመራጭ ከማድረግ ባለፈ ወጣቱ ከአልባሌ ቦታ እንዲታቀብ እያገዙ መሆናቸውን ተናግሯል፡፡ በወራቤ ከተማ እየተከናወነ ያለው የወንዝ ዳርቻ ልማት ለአካባቢው ነዋሪዎች ምቹ የመዝናኛ ስፍራ መፍጠሩን የተናገረችው ደግሞ ሌላኛዋ የከተማው ነዋሪ ወጣት አኒሳ ከድር ናት።   መዝናኛ ስፍራው ሠርግን ጨምሮ ሌሎች ማህበራዊ ኹነቶችን ማስተናገድ በሚያስችል መልኩ መገንባቱን ገልጻ፣ ልማቱን ለማስቀጠል የበኩሏን እንደምትወጣ አረጋግጣለች።
አየር መንገዱ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በመግዛት፣ በማንቀሳቀስ እና በመጠገን ረገድ በአፍሪካ ግንባር ቀደም ነው  
May 14, 2026 442
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በመግዛት፣ በማንቀሳቀስና በመጠገን በአፍሪካ ቀዳሚ መሆኑን ዋና ሥራ አስፈፃሚው አቶ መስፍን ጣሰው ገለጹ። አየር መንገዱ 80ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን ምክንያት በማድረግ ዛሬ የመሬት ላይ አውሮፕላን ትዕይንት (Static Air Show) አካሂዷል። አውሮፕላኖች ለሕዝብ ዕይታ የሚቀርቡበትን ትዕይንት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው ከፍተውታል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ አየር መንገዱ 80ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን ለማክበር የተለያዩ መርሃ ግብሮችን በማከናወን ላይ ይገኛል። ዛሬ የቀረበው የመሬት ላይ አውሮፕላን ትዕይንትም የዚሁ ክብረ በዓል አካል መሆኑን ገልጸዋል። ይህ መርሃ ግብር አየር መንገዱ በየዓመቱ 21 ሚሊዮን መንገደኞችን እና 850 ሺህ ቶን ጭነት ለማጓጓዝ የሚጠቀምባቸውን ዘመናዊ አውሮፕላኖች ለማህበረሰቡ ያስተዋወቀበት መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሁል ጊዜም ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶች የሆኑ አውሮፕላኖችን በመግዛት፣ በማንቀሳቀስ እና በመጠገን ረገድ በአፍሪካ ቀዳሚ መሆኑንም አረጋግጠዋል። ይህም አየር መንገዱን በአህጉሪቷ እጅግ ስኬታማ፤ በዓለም አቀፍ ደረጃም ዘመናዊና አዳዲስ አውሮፕላን ስብስብ (Young Fleet) ያለው ተወዳዳሪ አየር መንገድ እንዳደረገው ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት አየር መንገዱ 147 አውሮፕላኖች እንዳሉት የገለጹት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ አሁን ላይ እያደገ ከመጣው ፍላጎት አኳያ ቁጥሩ በቂ አለመሆኑን አስረድተዋል። ለዚህም ይረዳ ዘንድ ከቦይንግ እና ኤርባስ ኩባንያዎች ከ100 በላይ አውሮፕላኖች መታዘዛቸውን ጠቁመዋል። አየር መንገዱ በአምስት አህጉራት፣ በ82 ሀገራት እና በ140 መዳረሻዎች በረራ በማድረግ ሰዎችን በማገናኘትና ባህላዊ ትስስር በመፍጠር ረገድ አስደናቂ ሚና እየተወጣ እንደሚገኝም አብራርተዋል። አየር መንገዱ ላለፉት 80 ዓመታት ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በመጠቀም በአፍሪካ ሰማይ ላይ ቀዳሚ መሆኑን አመልክተው፤ ሀገራትን በማቀራረብና በዓለም አቀፍ የባህልና የንግድ ልውውጥ ረገድ ወሳኝ ሚና ሲጫወት መቆየቱን ዋና ሥራ አስፈፃሚው ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የታሪክ፣ የፅናት፣ የሀገር ግንባታ ውጤትና የአፍሪካውያን የትስስር ተምሳሌት ነው
May 14, 2026 335
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ አየር መንገድ የታሪክ፣ የፅናት፣ የሀገር ግንባታ ውጤትና የአፍሪካውያን የትስስር ተምሳሌት መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ 80ኛ ዓመት የምስረታ በዓልን ምክንያት በማድረግ የመሬት ላይ አውሮፕላን ትዕይንት (Static Air Show) መርሃ ግብር በአየር መንገዱ ቅጥር ግቢ አካሂዷል፡፡ እንዲሁም አየር መንገዱ በዓለም አቀፍ የባህል ልውውጥ ወሳኝ ሚና እየተወጣ መሆኑን የሚያንፀባርቅ ዓለም አቀፍ የባህል ቀን በስካይ ላይት ሆቴል አክብሯል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከተመሰረተ ጥቂት ወራት በኋላ የተቋቋመ ታሪካዊ ተቋም ነው፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም አቀፍና በአህጉር አቀፍ ደረጃ ህዝቦችን እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችን የማሳለጥ ተልዕኮ ሰንቆ መነሳቱን አስታውሰዋል፡፡ አየር መንገዱ ባለፉት አስርት ዓመታት አፍሪካን ከቀረው ዓለም ጋር ድልድይ ሆኖ በማገናኘት መንገደኞችና ሸቀጦችን አጓጉዟል፤ ንግድና ኢንቨስትመንት፣ ቱሪዝምና ዲፕሎማሲ እንዲሳለጥ አድርጓል ብለዋል፡፡ የአፍሪካ ቀዳሚ የአቪዬሽን ግሩፕ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ፈጣን እድገት እያስመዘገቡ ካሉ አየር መንገዶች አንዱ መሆን መቻሉንም ገልጸዋል፡፡ መንግስት ሁሉን አቀፍ ሪፎርም በማድረግ የዘርፉን መሰረተ ልማት በማዘመን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ የሀገራዊ ለውጥ አጀንዳ ማዕከል እንዲሆን አድርጓል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የኢኮኖሚ ስትራቴጂያዊ ምሰሶና የአፍሪካውያን የኩራት ምንጭ መሆኑን ጠቅሰው፤ በኢትዮጵያ በአቪዬሽንና ሎጂስቲክስ ያላትን መሪነት የሚያጠናክሩ ፖሊሲዎች ገቢራዊ እንደሚደረጉ ገልጸዋል፡፡ የአውሮፕላን ትዕይንቱ አየር መንገዱ ባለፉት ዓመታት ያስመዘገበውን የቴክኖሎጂ እድገትና የብቃት ጉዞ የሚያሳይ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ለአካባቢ ጥበቃ ተስማሚ የአቪዬሽን፣ ዘመናዊ የሎጂስቲክስ ስርዓት እና በአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ስር ወደላቀ አህጉራዊ ውህደት ለመሸጋገር በትጋት እንሰራለን ብለዋል፡፡ ለአየር መንገዱ ስኬታማ ጉዞ አስተዋጽኦ ላደረጉ የቀድሞና የአሁኑ መሪዎች፣ ፓይለቶች፣ መሐንዲሶችና ለመላው ሰራተኞች ምስጋና አቅርበዋል። አየር መንገዱ በአምስት አህጉራት፣ በ82 ሀገራት እና በ140 መዳረሻዎች በረራ በማድረግ ሰዎችን በማገናኘትና ባህላዊ ትስስር በመፍጠር ረገድ አስደናቂ ሚና እየተወጣ መሆኑ ይታወቃል። አየር መንገዱ ላለፉት 80 ዓመታት ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በመጠቀም በአፍሪካ ሰማይ ላይ ቀዳሚ ነው።
በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች በቤተሰብ ደረጃ በምግብ ራስን የመቻል ጥረትን እውን እያደረጉ ነው
May 14, 2026 148
ሀዋሳ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፡-በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች በቤተሰብ ደረጃ በምግብ ራስን የመቻል ጥረትን እውን እያደረጉ መሆኑን የሲዳማ ክልል የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ኃላፊ መምሩ ሞኬ ገለጹ። "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በግብርና ሚኒስቴር ትብብር የተዘጋጀ የውይይት መድረክ በሐዋሳ ከተማ ተካሄዷል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ኃላፊ መምሩ ሞኬ፤ በክልሉ አዳዲስ የግብርና ኢንሼቲቮች ተግባራዊ እየተደረጉ ይገኛሉ ብለዋል።   በተለይም በሰብል ልማት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም በእንስሳት ሀብት ልማት በስፋት ስለመሰራቱ አንስተዋል። በመሆኑም በክልሉ በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች በቤተሰብ ደረጃ በምግብ ራስን የመቻል ጥረትን እውን እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሸን ኮሚሽነር ወገኔ ብዙነህ፤ እንደ ሀገር የተያዙ በምግብ ራስን የመቻል ግቦችን በመከተል በክልሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ እና ውጤትም እየተገኘባቸው ነው ብለዋል።   በዚህም ከጥቂት ዓመት በፊት እህል ሲሰፈርላቸው የነበሩ በርካታ አርሶ አደሮች ከችግርና ድህነት የወጡ መሆኑን አንስተው በክልሉ የተጀመሩ የግብርና ልማት ኢንሼቲቮች በስፋት የሚቀጥሉ መሆኑን ተናግረዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር ለማ መሰለ (ዶ/ር)፤ በበኩላቸው በክልሉ ለአደጋ ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም የመገንባት ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል።   የክልሉን ልዩ ፀጋና አቅም በመለየት በተሰሩ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ለሀገር የተረፉ የግብርና ምርቶች እየተመረቱ ይገኛሉ ብለዋል።
ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን የቡና ላኪነት ሚና ይበልጥ ለማሳደግ ትኩረት ሰጥታለች
May 14, 2026 249
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን የቡና ላኪነት ሚና ይበልጥ ለማሳደግ የሚያስችል ስትራቴጂ ተግባራዊ በማድረግ በትኩረት እየሰራች መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ ገለጹ። ኢትዮጵያ በሚቀጥለው ዓመት የአፍሪካ ቡና ጉባኤን ለማስተናገድ የሚያስችላትን ስምምነት ከኢንተር-አፍሪካ የቡና ድርጅት (Inter-African Coffee Organization) ጋር ተፈራርማለች።   ስምምነቱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ እና የኢንተር-አፍሪካ የቡና ድርጅት ዋና ጸሐፊ አምባሳደር ሰለሞን ሩቴጋ ፈርመውታል። አምባሳደር ሀደራ በወቅቱ እንደገለጹት፤ አፍሪካ በቡና ምርት የታደለች አህጉር ብትሆንም ከዘርፉ ተገቢውን ጥቅም ሳታገኝ ቆይታለች። ቡና ለኢትዮጵያ የምጣኔ ሀብት ዕድገትን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች ሕይወታቸውን የሚመሩበት ዋና የግብርና ምርት መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በቡና ዘርፍ ውጤታማ የሚያደርጓትን የተለያዩ ተግባራት በትኩረት እያከናወነች እንደሚገኝ ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸው፤ እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን የቡና ላኪነት ሚና ለማሳደግ የሚያስችል ስትራቴጂን ተግባራዊ አድርጋ እየሠራች ነው ብለዋል። በዘርፉ የተሰማሩ አርሶ አደሮችን ምርታማነት ለማሳደግ፣ አቅማቸውን መገንባትና የቡና ጥራትን ማረጋገጥ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ለአብነት አንስተዋል።   ስምምነቱ ኢትዮጵያ ከኢንተር-አፍሪካ የቡና ድርጅት ጋር ያላትን ግንኙነት ይበልጥ የሚያጠናክር መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይም 25 ቡና አምራች የአፍሪካ ሀገራት የሚሳተፉበትን ይህንን ጉባኤ በተሳካ ሁኔታ ለማስተናገድ ኢትዮጵያ ሙሉ ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል። የኢንተር-አፍሪካ የቡና ድርጅት ዋና ጸሐፊ አምባሳደር ሰለሞን ሩቴጋ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ይህንን ትልቅ የአፍሪካ የቡና ጉባኤ ለማስተናገድ በመስማማቷ ድርጅታቸው የተሰማውን ከፍተኛ ደስታ ገልጸዋል። ዋና ጸሐፊው አክለውም፣ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላት የቡና ተወዳዳሪነትና ያካበተችው ሰፊ ልምድ ጉባኤው ስኬታማ እንዲሆን ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ያላቸውን እምነት ገልጸው፤ ለዝግጅቱ መሳካት ድርጅታቸው አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በአፍሪካ ውስጥ ኢትዮጵያን ጨምሮ 25 ቡና አምራች ሀገራት በተለያዩ ጊዜያት በመገናኘት የቡና ምርትና ምርታማነትን በተመለከቱ አጀንዳዎችና በዘርፉ ላይ በሚስተዋሉ ተግዳሮቶች ዙሪያ በመምከር የመፍትሔ አቅጣጫ ሲያስቀምጡ ቆይተዋል።   ኢትዮጵያ በሚቀጥለው ዓመት በቡና ዘርፍ ላይ የሚመክር ስብሰባ የምታስተናግድ መሆኗ ሀገሪቱ ከዘርፉ ማግኘት የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝና ልምዷን ለሌሎች ሀገራት እንድታካፍል ትልቅ በር ይከፍታል ነው ያሉት። በተጨማሪም አፍሪካውያን ነጻ የንግድ ቀጣናን ተጠቅመው እርስ በእርስ ቡና መገበያየት የሚችሉበትን ምቹ መድረክ እንደሚፈጥርም አመልክተዋል። ዝግጅቱ የሀገሪቱን የቱሪዝም ዘርፍ ከማነቃቃት ባለፈ የኢትዮጵያን ልዩ ልዩ የቡና ዝርያዎችና ባህላዊ የቡና አፈላል ሥርዓት ለዓለም ይበልጥ ለማስተዋወቅ መልካም አጋጣሚ እንደሚፈጥር አስገንዝበዋል።
ከተረጂነት የመውጣት ጉዳይ ሀገራዊ ክብርና ሉአላዊነትን የማረጋገጥ ወሳኝ ሀገራዊ አጀንዳ ነው
May 14, 2026 95
ሀዋሳ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፡-ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጂነት የመውጣት ጉዳይ የሀገርን ክብርና ሉአላዊነት የማረጋገጥ ወሳኝ አጀንዳ መሆኑን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በግብርና ሚኒስቴር ትብብር "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በሐዋሳ ከተማ የውይይት መድረክ ተካሂዷል።   በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) በወቅቱ፤ የኢትዮጵያ ክብርና ሉአላዊነት በፅኑ መሰረት ላይ ማኖር የሚቻለው በምግብ ራስን በመቻል ከተረጅነት መውጣት ሲቻል መሆኑን ገልጸው ከተረጅነት የመውጣት ጥረት የብሄራዊ ጥቅምና የሉአላዊነት ጉዳይ ነው ብለዋል። ከተረጂነት የመውጣት ጉዳይ የብሔራዊ ጥቅም አካል ሆኖ የመንግስት ስትራቴጂክ አጀንዳ ተደርጎ በፖሊሲ አቅጣጫ እየተመራ ይገኛል ነው ያሉት። በመሆኑም ምርታማነትን በማሳደግ የሀገርን ብልጽግና እውን በማድረግ የኢትዮጵያን የድህነት ታሪክ የመቀየር ጉዳይ በመንግስት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራበት ይገኛል ብለዋል። የሀገርን እምቅ ሃብቶች በማልማት የምርት አቅምን በማሳደግ ሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎችን በራስ አቅም የመመከት ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። የኢትዮጵያን ክብርና ሉአላዊነት አስጠብቆ ለመዝለቅ የተረጅነትና የልመና አስተሳሰብን በማስወገድ አልምቶና አምርቶ ብልጽግናዋን እውን ማድረግ ይገባል ብለዋል። የቤተሰብና የማህበረሰብ ብልፅግና ማረጋገጥና ሀገርን ከተረጅነትና ጥገኝነት ማላቀቅ የመንግስት የፖሊሲ አቅጣጫ ግቦች መካከል መሆኑንም ለአብነት ጠቅሰዋል። ከድህነት በመውጣት የሚደረገውን ጥረትና እንደ ሀገር የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት የሚደረገው ጥረት መቀጠሉን አንስተው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር ) በበኩላቸው፤ የሀገርን እምቅ ጸጋዎች በማልማት ምርታማነትን በማሳደግ ከራስ የተሻገረ ስኬት ማስመዝገብ እንደሚቻል የተመዘገቡ ውጤቶች ማሳያ ናቸው ብለዋል።   በተለያዩ የሀገሪቷ አካባቢዎች ባለፉት ጥቂት አመታት የመጡ ለውጦችና የተመዘገቡ ስኬቶች እምቅ አቅሞችን ወደ ተጨባጭ ውጤት መለወጥ ያስቻሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም በግብርናው ዘርፍ በተለያዩ ኢንሸቲቮች የተጀመሩ የልማት ጥረቶችን ዘላቂ በማድረግ ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጂነት የመውጣት ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ፤ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት መሻገር የሀገር ወሳኝ አጀንዳ መሆኑን አንስተው የኢትዮጵያን ተረጂነት ታሪክ የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል።   በተረጅነት ዙሪያ የዜጎች የአስተሳሰብ ለውጥ ወሳኝ መሆኑን አንስተው በዚህ ረገድ ሚዲያዎች የይዘት ስራዎችን በልዩ ትኩረት መስራት ይኖርባቸዋል ብለዋል።
የማዕድን ትሩፋት ለኢትዮጵያ ትንሳኤ
May 14, 2026 77
ባለፉት የለውጥ ዓመታት መንግሥት የማዕድን ዘርፍን ከነበረበት መዋቅራዊ ችግር በማውጣት ለሀገር ሁለንተናዊ ዕድገትና ለብሔራዊ ሉዓላዊነት ምሰሶ እንዲሆን ለማድረግ ቆራጥ እርምጃዎችን ወስዷል። ቀደም ሲል ዘርፉ ግልጽነት በጎደለው አሠራር፣ በሕገ-ወጥ ዝውውርና የጥቂቶች መጠቀሚያነት ተተብትቦ የቆየ ቢሆንም፣ በአሁኑ ወቅት ከ"እርግማን" ወደ "ልማት መሣሪያነት" ተቀይሯል። በመደመር መንግሥት ዕይታ የማዕድን ዘርፍ ልማት ለኢትዮጵያ የሰላም፣ የዕድገትና የብሔራዊ ሉዓላዊነት ምንጭ እንዲሁም ለዘላቂ ልማትና ለኅብረተሰብ ተጠቃሚነት ወሳኝ ምሰሶ ሆኖ ያገለግላል። ዘርፉን የኢኮኖሚው ምሰሶ ለማድረግ በተወሰደው የሪፎርም እርምጃ፣ የማዕድን ሀብት አስተዳደር ሥርዓቱ በቴክኖሎጂ እንዲደገፍና ተጠያቂነት የሰፈነበት እንዲሆን በማድረግ የኮንትሮባንድ ንግድን በከፍተኛ ሁኔታ መግታት ተችሏል። በተለይም ማዕድናትን በጥሬው የመላክ ልማድን በመቀየር፣ በሀገር ውስጥ የማዕድን ምርቶችን ዕሴት የሚጨምሩ ፋብሪካዎችንና የወርቅ ማጣሪያዎችን በመገንባት የውጭ ምንዛሬ ግኝታችን ወደ ላቀ ደረጃ ተሸጋግሯል። የወርቅ ወጪ ንግድን ለማሳደግ በተደረገው ጥረት በ2012 በጀት ዓመት 3.3 ቶን የነበረው ምርት በ2017 በጀት ዓመት ወደ 38.83 ቶን አድጓል። ይህም ከዘርፉ የሚገኘውን የውጭ ምንዛሬ ከ200 ሚሊዮን ዶላር ወደ 3.46 ቢሊዮን ዶላር ከፍ እንዲል አድርጎታል። ይህ ውጤት የተገኘው የኮንትሮባንድ መንገዶችን በቴክኖሎጂ በታገዘ መዋቅር በመዝጋትና የገበያ ሥርዓቱን በማዘመን ነው። በተጨማሪም ለኮንስትራክሽን ግብዓት የሚሆኑ እንደ ሲሚንቶ ያሉ ምርቶች በከፍተኛ ሁኔታ በአቅርቦት እንዲጨምሩ ተደርጓል። በአፍሪካ ግዙፍ የሆነውን የለሚ ሲሚንቶ ፋብሪካን ጨምሮ አዳዲስ ፋብሪካዎች ወደ ሥራ በመግባታቸው፣ የሲሚንቶ ምርት በ2014 ከነበረበት 6.2 ሚሊዮን ቶን በ2017 ወደ 9.1 ሚሊዮን ቶን ደርሷል። የሀገር ውስጥ ምርትን በመተካት ረገድም ትልቅ ስኬት ተመዝግቧል። ቀደም ሲል ለሲሚንቶ ምርት የሚያስፈልገው የድንጋይ ከሰል በመቶ ሚሊዮን ዶላሮች ከውጭ ይገባ የነበረ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት አራት የድንጋይ ከሰል ፋብሪካዎች ወደ ምርት ገብተው ምርቱን በሀገር ውስጥ መተካት ተችሏል። በተመሳሳይ ለዓመታት የሕዝባችን ምኞት የነበረው የካሉብ ጋዝ ሀብት ለልማት እንዲውል የተደረገ ሲሆን፣ ይህም ለማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ፣ ለትራንስፖርትና ለኃይል አቅርቦት የሚውልበት ሥርዓት እየተዘረጋ ይገኛል። ማዕድን በሚወጣባቸው አካባቢዎች ያሉ ማኅበረሰቦችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥም መንግሥት የሮያሊቲ ክፍያ እና ታክስን ግልጽ እና ፍትሐዊ በሆነ ቀመር እንዲያገኙ አድርጓል። ይህም የማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሠረተ ልማቶች እንዲስፋፉና ባሕላዊ አምራቾች ወደ ተሻለ የሥራ ዘዴ እንዲሸጋገሩ ዕድል ፈጥሯል። መንግሥት ዘርፉን ለሀገራዊ ኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን እንዲውል ግልጽ የፖሊሲ አቅጣጫ አስቀምጦ እየመራው ይገኛል። በአካባቢ ጥበቃ ረገድም ጠንካራ የቁጥጥር ዐቅምና የሕግ ማሕቀፍ በመገንባት ተፈጥሮን የመጠበቅ ሥራ በትኩረት እየተከናወነ ይገኛል። በሚቀጥሉት ዓመታት ለሀገራችን ብልፅግና ስትራቴጂያዊ ጠቀሜታ ባላቸው ማዕድናት ላይ ሰፊ ጥናትና ምርምር እንዲደረግ ትኩረት ይሰጣል። በተለይም በማዳበሪያ ፋብሪካ ላይ የተጀመረው ጥረት በፔትሮ-ኬሚካልና በተያያዥ ፕሮጀክቶች እንዲቀጥል ይደረጋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ተፈላጊ የሆኑ እንደ ሊቲየም ያሉ ብርቅዬ ማዕድናት ለሀገራችን የኢኮኖሚ ዕድገትና ለቴክኖሎጂ ፈጠራ እንዲውሉ በቁርጠኝነት ይሠራል። የማዕድን አካባቢዎች ሰላማዊ፣ የአካባቢውን ሕዝብ ተጠቃሚ የሚያደርጉና በሕግ የሚመሩ እንዲሆኑ ይደረጋል። እስካሁን በተከናወኑ ሥራዎች የማዕድን ሀብታችን ለኢትዮጵያ የማንሰራራት ዘመን አብነት እንዲሆን መሠረት ጥሏል። ይህ የተቀናጀ መሪነት ማዕድን ለኢትዮጵያ የሰላም፣ የዕድገትና የብሔራዊ ሉዓላዊነት ምንጭ እንዲሆን መሠረት ጥሏል።
በኢትዮጵያ እየተከናወኑ ያሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ከተረጅነት የመውጣት ጥረትን ለማሳካት የሚያስችል ተጨባጭ ውጤት እያመጡ ነው
May 14, 2026 80
ሀዋሳ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ እየተከናወኑ ያሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ከተረጅነት የመውጣት ጥረትን ለማሳካት የሚያስችል ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እውነቴ አለነ ገለጹ። "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በግብርና ሚኒስቴር ትብብር የተዘጋጀ የውይይት መድረክ በሐዋሳ ከተማ ተካሂዷል።   በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እውነቴ አለነ፣ ሀገራዊ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት የመውጣት ጥረት ተጨባጭ ውጤት እያመጣ መሆኑን ገልጸዋል። በግብርና ልማት በተለይም የስንዴ ምርታማነትን በማሳደግ ከራስ አልፎ ለውጭ ገበያ በማቅረብ የተመዘገበውን የላቀ ስኬት ለአብነት ጠቅሰዋል። በሌሎች የተለያዩ የግብርና ልማት ስራዎችን በተጠናከረ መልኩ በማከናወን ምርታማነትን በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። የሀገር በቀል የምጣኔ ሃብት ማሻሻያ በማድረግ በሁሉም ሴክተሮች የተከናወኑ የልማት ስራዎችም ሀገራዊ እመርታና ማንሰራራት ማምጣት ያስቻሉ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም ሀገራዊ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት የመውጣት ጥረት ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ይገኛል ብለዋል። በኢትዮጵያ እየተከናወኑ ያሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ከተረጅነት የመውጣት ጥረትን ለማሳካት የሚያስችል ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ዋና ስራ አስፈፃሚ ሠይፈ ደርቤ፤ በበኩላቸው እንደ ሀገር በምግብ ራስን ለመቻል የተጀመረው ግብ እንዲሳካ በቂ ግንዛቤ መፍጠር አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል። ለዚህም ሚዲያ የማይተካ ሚና ያለው መሆኑን ገልጸው ኢዜአ ይህንን ሀገራዊ ትልም ለማሳካት የይዘት ስራዎችን በስፋት ተደራሽ የማድረግ ጥረቱን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ከተረጅነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ለማሳካት የሚደረገው ጥረት እንዲሳካ ኢዜአ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በመድረኩ ላይ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)፣ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ እና የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) እንዲሁም ሌሎችም የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና የዘርፉ ባለሙያዎች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያን ከተረጂነት ወደ አምራችነት ፤ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ጉዞ
May 14, 2026 91
የመደመር መንግስት የኢኮኖሚ እሳቤ የሀገራችንን ግብርና በተሟላ መልኩ ለማዘመን የሚያስችል ትልቅ ራዕይ ላይ የተመሠረተ ነው። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ለዘመናት ከድህነት አዙሪት መውጣት ያልቻለው የምርት ሂደቱ ከዝናብ ጥገኝነት እና ከኋላቀር አሠራር ባለመላቀቁ እንደሆነ ይታመናል ። የግብርናው ዘርፍ ማሻሻያ ዋና ግብ የዜጎችን ክብር ከፍ የሚያደርግና ሀገራዊ የምግብ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥ እንዲሆን ተደርጓል። ለዚህም የገጠሩን ማኅበረሰብ ሕይወት ለመለወጥና ሀገራዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ ኢንደስትሪያላይዜሽንና የግብርና ትራንስፎርሜሽን እንደ ዋና መሠረት ተቀምጠዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት መንግሥት የግብርናውን ኋላቀር ሂደት በመቀየር ቴክኖሎጂን እንደ ዋና ግብዓት በመጠቀም ረገድ ትልቅ የታሪክ እጥፋት ፈጥሯል። ይህም ግብርናው ከልመናና ከችሮታ ወጥቶ የኢኮኖሚው ዋና ሞተር እንዲሆን አስችሎታል። በተለይም አርሶ አደሩን ወደ ገበያ-ተኮር ምርት በማሸጋገር፣ የሥነ-ምግብ ዋስትናን በማረጋገጥና ለሚሊዮኖች የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ተጨባጭ ውጤቶች ተመዝግበዋል። በኢኮኖሚ ማሻሻያው አማካኝነት ግብርናን የኢንዱስትሪ ጥሬ ዕቃ ግብዓት በሀገር ውስጥ ምርት ለመተካትና ለውጭ ገበያ ጥራት ያለው ምርት ለማቅረብ ጠንካራ መሠረት ተጥሏል። በመንግሥት የተቀናጀ ጥረት የተገኙ ውጤቶችም የሚያበረታቱ ናቸው። በ2013 በጀት ዓመት 17.2 ሚሊዮን ሄክታር የነበረው የታረሰ መሬት፣ በ2017 በጀት ዓመት ድግግሞሽን ጨምሮ ወደ 32.2 ሚሊዮን ሄክታር አድጓል። በዚህም ጠቅላላ የሰብል ምርት ከ356.6 ሚሊዮን ኩንታል ወደ 836.4 ሚሊዮን ኩንታል ከፍ ብሏል። "የትኛውም መሬት ፆም አያድርም" በሚል መርህ በተከናወነ ሥራ፣ በ2017 የምርት ዘመን አጠቃላይ የግብርና ምርት 1.57 ቢሊዮን ኩንታል ደርሷል። በተለይም የስንዴ ምርት በየዓመቱ የ49 በመቶ ዕድገት በማሳየት፣ ሀገሪቱ የምግብ ሉዓላዊነቷን ከማረጋገጥ ባለፈ ስንዴን ለውጭ ገበያ ማቅረብ አስችሏታል ። ከዚህ በተጨማሪ የሩዝ ምርት ከ3 ሚሊዮን ኩንታል ወደ 63 ሚሊዮን ኩንታል፣ የቡና ምርት ደግሞ ወደ 11.5 ሚሊዮን ኩንታል አድጓል። መንግሥት በይፋ ተግባራዊ ያደረገው "የሌማት ትሩፋት" መርሃ-ግብር የእንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርትን በማሳደግ ረገድ ተምሳሌታዊ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። በወተት፣ በዶሮ፣ በማርና በዓሳ ልማት የታየው ውጤት የኢኮኖሚ ነፃነትን ለማረጋገጥ ዓይነተኛ ድርሻ አለው። በተመሳሳይ በከተማ ግብርና ረገድ የተከናወኑ ተግባራት የከተሞችን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ፣ የጓሮ ሜዳዎችንና የሕንፃ ጣራዎችን ለምርታማነት እንዲውሉ በማድረግ የኑሮ ውድነትን ለመቋቋም እና ለወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክተዋል። ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት መንግሥት ግብርናን ማዘመንና የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫው አድርጓል። ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ማስፋፋት፣ የግብርና ፋይናንስ አቅርቦትን ማሻሻልና የግል ዘርፉን ተሳትፎ ማሳደግ ትኩረት የሚሰጣቸው ጉዳዮች ናቸው። የመስኖ አቅምን በማጎልበት ግብርናን ከዝናብ ጥገኝነት የማላቀቅ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል። እንዲሁም "ከእርሻ እስከ ጉርሻ" ያለውን የዕሴት ሰንሰለት ለማዘመን ዲጂታል ቴክኖሎጂንና ሜካናይዜሽንን በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ታቅዷል። መንግሥት የጀመረውን የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ በማጠናቀቅ ግብዓቱን በሀገር ውስጥ ለማምረት በዝግጅት ላይ ይገኛል። ዛሬ የተመዘገቡት ውጤቶች የነገው ብሩህ ጉዞ መሠረት ናቸው። መንግሥት ኢትዮጵያን ከተረጂነት ወደ አምራችነት፣ ከምግብ ዋስትና ወደ ሁለንተናዊ ብልፅግና ለማሸጋገር የገባውን ቃል በተግባር እየፈጸመ ይገኛል።
ባለፉት 10 ወራት ከወጪ ንግድ 8 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቷል
May 14, 2026 240
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፦ባለፉት 10 ወራት ከወጪ ንግድ 8 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘት መቻሉን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ምርት ገበያ (ECX) በግብርና ምርቶች የኤክስፖርት ቢዝነስ እንዲሁም በቡና ቅምሻና ደረጃ አወጣጥ ዘርፍ ለሦስት ወራት ያሰለጠናቸውን ባለሙያዎችን በዛሬው ዕለት አስመርቋል።   የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ ዘመናዊና ውጤታማ የወጪ ንግድ ሥርዓት ለመገንባት በዕውቀትና በክህሎት የዳበረ የሰው ኃይል ማፍራት ወሳኝ ነው። በዚህም የኢትዮጵያ ምርት ገበያ አካዳሚ ብቁ ባለሙያዎችን በማፍራት ረገድ አበረታች ተግባር እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በወጪ ንግድ አስደናቂ ለውጦች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፤ በተለይም በያዝነው የ2018 በጀት ዓመት አበረታች ውጤት መገኘቱን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት 10 ወራት ከወጪ ንግድ 8 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘት መቻሉን ተናግረው እስከ በጀት ዓመቱ መጨረሻ ድረስ ደግሞ ገቢውን ወደ 10 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ታቅዶ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡   የዛሬዎቹ ሰልጣኞች ይህንን ሀገራዊ የገቢ ግብ ለማሳካትና የወጪ ንግዱን በዕውቀትና በክህሎት ለመምራት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ እንደሚኖራቸውም አመላክተዋል። ተመራቂዎቹም ያገኙትን ዕውቀት ተጠቅመው የኢትዮጵያ የወጪ ንግድ ምሰሶ ሆነው እንዲሰሩ አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ምርት ገበያ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መርጊያ ባይሳ በበኩላቸው፤ የወጪ ንግድ በዘመናዊ ግብይት ሥርዓት፣ በዕውቀትና በሰለጠነ የሰው ኃይል እንዲመራ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡   ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የወጪ ንግድ ያላትን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ጥራት ያለው ምርት ለገበያ ማቅረብ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። ለዚህም ለወጪ ንግድ ስኬት ቁልፍ በሆኑት የደረጃ አወጣጥና የጥራት ቁጥጥር ስልጠናዎች በምርት ገበያ አካዳሚ ሥልጠና እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። አካዳሚው ከ2015 ዓ.ም ጀምሮ በቡና ቅምሻ ዘርፍ ብቻ ከ3ሺህ 200 በላይ ሰልጣኞችን አሰልጥኖ ያስመረቀ ሲሆን በዘንድሮው ዓመት በግብርና ምርቶች ኤክስፖርት ቢዝነስ እና በቡና ደረጃ አወጣጥ 168 ባለሙያዎች ማስመረቁን አስታውቀዋል። የምርት ገበያው አካዳሚ እያስመዘገበ ያለው ስኬት ከሀገር ውስጥ አልፎ አህጉራዊ እውቅናን እያገኘ መምጣቱን የገለጹት አቶ መርጊያ፣ እስካሁን ከ8 በላይ የአፍሪካ ሀገራት የአካዳሚውን ተሞክሮና ልምድ መቅሰማቸውን ጠቁመዋል። አስተያየታቸውን የሰጡ ተመራቂዎች ስልጠናው በዘርፉ የነበራቸውን የተግባር ክፍተት የሞላ፣ ዓለም አቀፍ የገበያ መርሆዎችን በጥልቀት የተረዱበት መሆኑን ተናግረዋል። አስተያየት የሰጠችው ናርዶስ ተክሌ እንደገለጸችው፤ ስልጠናው ከዚህ ቀደም በልምድ ላይ ተመስርታ ትሠራው የነበረውን አሠራር በሳይንሳዊ የጥራት ደረጃና በቅምሻ ዕውቀት ለመተካት እንደሚያስችላት ገልጻለች፡፡ ተመራቂ ሁሴን አህመድ በበኩሉ፤ ስልጠናው የወጪ ንግድ ሂደቶችን፣ የህግ ማዕቀፎችንና የገበያ ትስስር ስልቶችን በጥልቀት ለመረዳት እንዳስቻለው ተናግሯል።
አዋጁ የህብረት ስራ ማህበራት ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያበረክቱትን አስተዋፅኦ የሚያሳድግ ነው
May 14, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፦ የህብረት ስራ ማህበራት ማሻሻያ አዋጅ የማህበራቱን ተወዳዳሪነትና ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያበረክቱትን አስተዋፅኦ የሚያሳድግ መሆኑን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ገለፀ። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው አምስተኛ ዓመት የስራ ዘመን 21ኛ መደበኛ ስብሰባ የህብረት ስራ ማህበራት ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል።   የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ፤ የማሻሻያ ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ ባቀረቡት ሪፖርትና የውሳኔ ሐሳብ በረቂቅ አዋጁ ዙሪያ በርካታ የባለድርሻ አካላትና የአስረጂ መድረክ መካሄዱን አንስተዋል። ነባሩ አዋጅ 985/2009 ከሀገሪቱ አሁናዊ ነባራዊና የሪፎርም ሂደት ጋር ያልተጣጣመ ነው ብለዋል። የህብረት ስራ ማህበራት ጠንካራ የውስጥ አመራርና የአስተዳደር ስርዓት ያለመኖር እንዲሁም ዘመናዊ የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓት ያለመተግበር ችግር ይስተዋልባቸው እንደነበር አንስተዋል። የማሻሻያ አዋጁ የተበታተኑና ውጤታማ ያልሆኑ በርካታ የህብረት ስራ ማህበራት ሰብሰብ ብለው እንዲደራጁና ትርፋማ የሚሆኑበት አሰራር እንዲዘረጉ የሚያስችል ነው ብለዋል። የህብረት ስራ ማህበራት ያለባቸውን የፋይናንስ አቅርቦት እጥረት በመፍታት ከፋይናንስ ተቋማት ጋር እንዲሁም የእርስ በርስ ትስስራቸውን የሚያጠናክር መሆኑንም ተናግረዋል። ብልሹ አሰራርና ብክነትን ለማስተካከል የሚያስችል የቁጥጥርና ተጠያቂነት አሰራርን እንደሚያጠናክር ነው ያነሱት። የህብረት ስራ ማህበራት ለሀገር ኢኮኖሚ ያላቸውን አስተዋፅኦ እንደሚያሳድግና የኦዲት ስርዓታቸውን እንደሚያጠናክር በማንሳት፥ ምክር ቤቱ የአዋጁን አስፈላጊነት በመገንዘብ እንዲያፀድቀው ጠይቀዋል። የምክር ቤቱ አባላት አዋጁ አሳሪ አሰራሮችን የሚፈታና የህብረት ስራ ማህበራት ከፋይናንስ ተቋማት ጋር ያላቸውን ትስስር እንዲሁም የማህበራቱን እርስ በርስ ትብብር የሚያጠናክር መሆኑን ገልፀዋል። በዚህም የህብረት ስራ ውስጥ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት የሚፈልግ ግለሰብና ተቋም ድርሻ እንዲሁም በማህበራት አመራርነት ላይ ስለሚኖር አካታችነት ድርሻ የተመለከቱ ጥያቄዎች አቅርበዋል።   የኢትዮጵያ ህብረት ስራ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሺሰማ ገብረ ሥላሴ፤ አዋጁ ሲዘጋጅ የሌሎች ሀገራት ተሞክሮን በመውሰድ የተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል። የኢንቨስትመንት ድርሻን በተመለከተ በሰጡት ምላሽ ማህበራትን የበለጠ ውጤታማ ለማድረግ ትብብርን ማጠናከር ወሳኝ በመሆኑ የተካተተ ነው ብለዋል። የማህበራት አመራር አካታችነት ባሉት የአባላት ቁጥር እንደሚወሰንና የሴቶች፣ አካል ጉዳተኞችና ወጣቶች ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ ናቸው። በዚህም መሰረት ምክር ቤቱ የቀረበውን ረቂቅ አዋጅ ቁጥር 1416/2018ን በሙሉ ድምፅ አፅድቋል።
በክልሉ መንግስት የገባውን ቃል በመተግበር የህዝቡን የልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ እየመለሰ ነው  
May 14, 2026 109
ጂንካ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፦ የክልሉ መንግስት የገባውን ቃል በመተግበር የህዝቡን የልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ እየመለሰ መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ አለማየሁ ባውዲ ገለጹ። በክልሉ የአሪ ዞን ሰሜን አሪ ወረዳ ከ 57 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት የተገነቡ የንፁህ መጠጥ ውሃና የሳላ ወንዝ ድልድይ ግንባታ ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል።   በፕሮጀክቶቹ ምረቃ ላይ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ አለማየሁ ባውዲን ጨምሮ የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብረሃም አታ እና ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል። በወቅቱም ዋና አፈ-ጉባኤ አለማየሁ ባውዲ እንደገለፁት መንግስት የገባውን ቃል በመተግበር የህዝቡን የልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ እየመለሰ ነው።   ዛሬ ለአገልግሎት የበቁት የሳላ ወንዝ ድልድይ እና የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች በህዝቡ ዘንድ ለረጅም ዓመታት ጥያቄ ሲነሳባቸው የነበሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። መንግስት የህዝቡን ጥያቄ በመገንዘብ አፋጣኝ መፍትሔ ለመስጠት ርብርብ ሲያደርግ እንደነበር ገልፀው፥ ለዚህም ዛሬ የተመረቁ ፕሮጀክቶች ማሳያ እንደሆኑም አመልክተዋል። የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም አታ በበኩላቸው አካባቢው ስንዴ፣ የቅባት እህሎች፣ ቅመማ ቅመምና ፍራፍሬዎች በስፋት የሚመረቱበት በመሆኑ የመንገድ ግንባታው ለማህበረሰቡ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ትልቅ ሚና አለው ብለዋል።   በተጨማሪም በአካባቢው ቀደም ሲል ከህብረተሰቡ ጥያቄዎች ሲነሳባቸው የነበሩ የጎዛ ጊቻ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት፣ የጎዞ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤትና ጎዛ ጤና ጣቢያ ግንባታዎች ተመርቀው ወደ አገልግሎት ገብተዋል ብለዋል። በቀጣይም የመብራት እና ሌሎች የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ምላሽ እንደሚያገኙ አረጋግጠዋል። በሰሜን አሪ ወረዳ የጎዛ ከተማ ነዋሪዎችም፤ በከተማው መብራት፣ ንፁህ የመጠጥ ውሃ፣ የመንገድ፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እና ጤና ጣቢያ እንዲገነቡ ሲጠይቁ መቆየታቸውን ገልጸዋል።   ከጥያቄዎቹ መካከል ንፁህ የመጠጥ ውሃ፣ የሳላ ወንዝ ድልድይ፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እና የጤና ጣቢያ ግንባታዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት በመብቃታቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም