ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር የተሰማሩ ወጣቶች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ነው
Apr 24, 2026 43
ጎንደር፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በጎንደር ከተማ በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር በወተት ሀብት ልማት የተሰማሩ ወጣቶች ሀብትና ጥሪት በማፍራት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደግ መቻላቸውን ተናገሩ።   ወጣት አስናቀ አብተው ለኢዜአ እንደገለጸው፤ በሁለት ላሞች የጀመረውን የወተት ሀብት ልማት ሥራ ይህን አሃዝ አሁን ወደ 17 አሳድጓል። የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብሩ ሠርቶ መለወጥ የሚለውን ህልሜን ለማሳካት ረድቶኛል፤ በአሁኑ ወቅትም ለዘጠኝ ሰዎች የሥራ ዕድል ፈጥሬያለሁ ብሏል። በቀን ከ200 ሊትር በላይ ወተት ለገበያ በማቅረብም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ማሳደጉን ጠቅሷል።   በቀን ከ100 ሊትር በላይ ወተት ለገበያ በማቅረብ ላይ የሚገኘው ወጣት ዓለሙ ሲሳይ በበኩሉ፤ በአንዲት ላም የጀመረውን የወተት ሃብት ልማት ሥራ በአሁኑ ወቅት ወደ ሥድስት የሚታለቡ ላሞች ከፍ አድርጓል። የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር የአካባቢ ጸጋዎችን ለይቶ በመጠቀም ከራስ አልፎ ለሌሎችም የሥራ ዕድል በመፍጠር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያሳድግ መሆኑን በተግባር ማረጋገጡንም ገልጿል።   መርሐ-ግብሩ የወጣቱን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በተጨባጭ የሚያረጋግጥና በአጭር ጊዜ ሠርቶ መለወጥ እንደሚቻል የሚያመላክት የተግባር ትምህርት ቤት ነው ያለው ደግሞ ወጣት አምሳሉ አካሌ ነው፡፡ በወተት ሀብት ልማት ዘርፍ በመሰማራት ከአራት ላሞቹ የሚያገኘውን የወተት ምርት እሴት ጨምሮ ለገበያ በማቅረብ ራሱንና ቤተሰቡን በተሻለ መንገድ ማኖር እንደቻለም ነው ያመለከተው።   የጎንደር ከተማ አሥተዳደር እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ መላኩ ደምሌ፤ ባለፉት ሶስት ዓመታት ተግባራዊ የተደረገው የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር ለወጣቱ ሰፊ የሥራ እድል ለመፍጠር አስችሏል ብለዋል፡፡ የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችንና ግብዓቶችን በመጠቀም የወተት ምርትን በማሳደግ በኩል 12 ቴክኒሻኖችን በማሰልጠን ከ14 ሺህ በላይ ላሞችን የማዳቀል ሥራ መከናወኑንም አብራርተዋል። በወተት ሀብት ልማት ዘርፍ የሚታየውን የእንስሳት መኖ እጥረት ለማቃለል እንዲቻልም በሰአት 30 ኩንታል የእንስሳት መኖ ማዘጋጀትና ማቀናበር የሚችል ዘመናዊ ፋብሪካ ማቋቋም መቻሉን አስረድተዋል፡፡   በከተማው በወተት ሀብት ልማት፣ በንብ ማነብ፣ በዶሮ እርባታና በእንስሳት ማድለብ እንዲሁም በዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ በክላስተር የተደራጁ ከ25 በላይ ኢንተርፕራይዞች ተቋቁመው ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመዋል።፡
ለዜጎች በርካታ የሥራ ዕድል እየፈጠረ የሚገኘው አምራች ኢንዱስትሪ
Apr 24, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በአምራች ኢንዱስትሪዎች በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ከመሆናቸው ባሻገር ዕውቀትና ክኅሎታቸውን እያሳደጉ መሆኑን በተለያዩ ፋብሪካዎች የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ወጣቶች ገለጹ፡፡ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ትኩረት ከሰጣቸው ዋና ዋና ዘርፎች መካከል የአምራች ኢንዱስትሪውን ዐቅም ማሳደግ አንዱ ነው።   ይህም በዋናነት የውጭ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የውጭ ምንዛሪን ለማዳን ያለመ ነው። ይህንን ተከትሎ በተከናወነው ተግባር ከዚህ ቀደም ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ይወጣባቸው የነበሩ ምርቶች በሀገር ውስጥ እንዲመረቱ በማድረግ ረገድ ተጨባጭ ውጤቶች እየተመዘገቡ ይገኛሉ። በተለይም ተኪ ምርቶችን በስፋት በማምረት ለሀገር ውስጥ ገበያ ከማቅረብ ባለፈ፤ ወደ ውጭ በመላክ ተጨማሪ የውጭ ምንዛሪ ከማግኘት አንጻር ከፍተኛ ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል። አምራች ኢንዱስትሪው ለወጣቶችና ለሴቶች ሰፊ የሥራ ዕድል እየፈጠረ ሲሆን፤ የቴክኖሎጂና የዕውቀት ሽግግር እንዲኖር በማድረግ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ በማሻሻል ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተም ይገኛል፡፡ ኢዜአ በተለያዩ ኢንዱስትሪዎች በመዘዋወር ያነጋገራቸው የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ተጠቃሚዎች እንዳሉት፤ በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል ተጠቅመው ኑሯቸውን እየለወጡ ነው።   በጎበዝ ማኑፋክቸሪንግ ኤሌትሪክ ኢንዱስትሪ የምትሠራው ቅድስት አስማማው እንዳለቸው፤ በተፈጠረላት የሥራ ዕድል ገቢ ከማግኘቷ በተጨማሪ ክኅሎቷን እያሳደገላት ይገኛል። ሌላኛው የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ታምራት ተሰማ በበኩሉ፤ የአምራች ኢንዱስትሪዎች መስፋፋትን ተከትሎ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ከማድረጉ በተጨማሪ የዕውቀትና ቴክኖሎጂ ሽግግርን በማሳለጥ ረገድ ትልቅ ድርሻ እንዳለው ተናግሯል።   ይህንንም ተከትሎ ከዚህ በፊት በሌሎች ኢንዲስትሪዎች ከነበረው ልምድ አሁን ላይ በተሻለ ቴክኖሎጂ ራሱን ብቁ ማድረግ አንስቶ በፋብሪካው በሚከፈለው ክፍያ ራሱን ከማስተዳደር አልፎ ቤተሰብም እየደገፈ እንደሚገኝ ገልጿል፡፡ በዳቼ ማኑፋክቸሪንግ የምግብ ማቀነባበሪያ ፋብሪካ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ የሆነው እዮብ ዱሬሳ በበኩሉ በድርጅቱ የሥራ ልምድ ማግኘት መቻሉን ገልጾ፤ በሚከፈለው ክፍያም ከራሱ አልፎ ቤተሰቦቹን መደገፍ መቻሉን ተናግሯል፡፡   በዚሁ ፋብሪካ በተፈጠረላት የሥራ ዕድል የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቷ ማደግ እንደቻለ የገለጸችው ደግሞ ሌላኛዋ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ አሚራ ጀማል ናት።   በሁዋጃን ልዩ ኢኮኖሚክ ዞን የጎበዝ የፀሐይ ኃይል ሶላር ሴል ማምረቻ ሥራ አስኪያጅ በረከት ኃይሉ፤ መንግሥት ለኢንዱስትሪ ዘርፉ በፈጠረው ምቹ ምኅዳር ምርታቸውን ለተለያዩ ሀገራት እየላኩ መሆኑን ተናግረዋል።   በመንግሥት እየተደረገ ያለው ድጋፍ የማምረት ዐቅማቸውን እንዳሳደገውም ገልጸዋል። ድርጅቱ ከ600 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩንም አስረድተዋል። የዳቼ የምግብ ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ፕላንት ማኔጀር ዐቢይ በቀለ በበኩላቸው፤ ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት ትልቅ ዕድል እየፈጠረላቸው መሆኑን ይናገራሉ፡፡   መንግሥት በየጊዜው በሚያደርግላቸው ድጋፍና ክትትል ምርቶቻቸውን በጥራትና በፍጥነት በማምረት ወደገበያ ተዳራሽ ለማድረግ እንዳስቻላቸውም አንስተዋል። አሁን ላይ ድርጅቱ በአራት ፋብሪካዎች 46 ዓይነት የታሸጉ ምግቦችን እያመረተ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እያቀረበ መሆኑንም አረጋግጠዋል። ፋብሪካው ሥራ ሲጀምር በ40 ሠራተኞች ብቻ መጀመሩን አውስተው፤ መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረትም ውጤታማ መሆን በመቻሉ አሁን ላይ ከ1 ሺ 300 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ተናግረዋል፡፡
በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ ቀርቧል  
Apr 24, 2026 79
ጅማ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለገበያ መቅረቡን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ተናገሩ። ኃላፊው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የሚመረተው የቡና ምርት ጥራቱን በጠበቀ መልኩ ለገበያ እየቀረበ ነው፤ አቅርቦቱም በየዓመቱ እያደገ መጥቷል። ለአርሶ አደሩ በየጊዜው የሚደረገው ድጋፍ፣ ክትትልና ሥልጠና የቡና ጥራትን በተሻለ ሁኔታ መጠበቅ እንዳስቻለም ገልጸዋል። ዘንድሮ 300 ሺህ ቶን የቡና ምርት መሰብሰቡን ገልጸው፤ ከዚህ ውስጥ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 52 ሺህ ቶን ቡና ለሀገር ውስጥና ለውጪ ገበያ ማቅረብ ተችሏል ብለዋል።   ጥራት ያለው ቡናን ለገበያ በማቅረብ ሂደት ውስጥ መሠረታዊ የኅብረት ሥራ ማኅበራት ድርሻ የላቀ መሆኑንም አመላክተዋል። የጅማ ዞን የኅብረት ሥራ ማኅበራት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ድማሙ ንጋቱ በበኩላቸው፤ በዞኑ 1 ሺህ 300 መሠረታዊ የኅብረት ሥራ ማኅበራትና 4 ዩኒየኖች እንደሚገኙ ገልጸዋል። በቡና ምርት ላይ የተሰማሩ ዩኒየኖች በቡና ጥራትና አቅርቦት ላይ በትኩረት እየሠሩ መሆኑን ተናግረዋል። ዘንድሮ 4 ሺህ 800 ቶን የታጠበና ስፔሻሊቲ ቡና ለዓለም ገበያ ለማቅረብ ታቅዶ፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የዕቅዱን 60 በመቶ ማቅረብ መቻሉን አረጋግጠዋል።
ከአፍሪካ አቪዬሽን መሪነት እስከ አህጉራዊ የኢኮኖሚ ትስስር
Apr 23, 2026 197
በሙሴ መለሰ ኢትዮጵያ በአፍሪካ የአቪዬሽን ታሪክ ታይቶ የማይታወቅና በአህጉሪቱ ትልቁ የሆነውን የ12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ግዙፍ የኤርፖርት ግንባታ ፕሮጀክት በቢሾፍቱ ከተማ በይፋ መጀመሯን የኢትዮጵያ አየር መንገድ አስታውቋል። ጋዜጠኛ ዳንኤል ኦሊቫሬስ ጋሌጎ በሲኤንኤን የጉዞ ገጽ ላይ ባሰፈረው ጽሁፍ እንደገለጸው፣ ይህ ሜጋ ፕሮጀክት አፍሪካውያን ተጓዦች ከአህጉሩ ውጭ ባሉ እንደ ዱባይ፣ ፓሪስና ለንደን ባሉ ማዕከላት በኩል የሚያደርጉትን አድካሚ ጉዞ በማስቀረት፣ አዲስ አበባን የአህጉሪቱ ቀዳሚ የመገናኛ ማዕከል ለማድረግ ያለመ ነው። ከአዲስ አበባ ከተማ በስተደቡብ ምስራቅ 48 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘው ይህ ግዙፍ ግንባታ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ታሪክ ትልቁ የአቪዬሽን መሰረተ ልማት ተብሎ መጠቀሱን ጋዜጠኛው በዚሁ ጽሁፉ አመልክቷል።   ስራው በይፋ የተጀመረው ባለፈው ጥር ወር ሲሆን፣ አውሮፕላን ማረፊያው በ2023 ዓ.ም (2030 እ.ኤ.አ) የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታው ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር፣ በዓመት 60 ሚሊዮን መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም እንደሚኖረው በሲኤንኤን የጉዞ ገጽ ላይ ተመልክቷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው ለጋዜጠኞች በሰጡት ማብራሪያ፣ ፕሮጀክቱ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ በዓመት እስከ 110 ሚሊዮን መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል። ይህም አውሮፕላን ማረፊያውን በዓለም ላይ በርካታ ተጓዦችን ከሚያስተናግደው የአትላንታው ሀርትስፊልድ-ጃክሰን አውሮፕላን ማረፊያ ካለው አቅም በላይ እንደሚያደርገው ዳንኤል ኦሊቫሬስ ጋሌጎ ባሰፈረው ጽሁፍ አብራርቷል። አውሮፕላን ማረፊያው ከመንገደኞች አገልግሎት ባለፈ፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠናን (AfCFTA) በላቀ ሁኔታ ለመደገፍ ታቅዶ የተገነባ መሆኑን ጋዜጠኛው በሲኤንኤን የጉዞ ገጽ ላይ ባሰፈረው ጽሁፍ በዝርዝር አስቀምጧል።   በዓመት 3 ነጥብ 73 ሚሊዮን ቶን ጭነት የማስተናገድ አቅም ያለው ይህ መሠረተ ልማት፣ በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ በከፍተኛ ፍጥነት እያደገ የመጣውን የአፍሪካን የጭነት በረራ ፍላጎት በሚገባ ምላሽ መስጠት የሚችል መሆኑን ተጠቁሟል። የአውሮፕላን ማረፊያው የተርሚናል ዲዛይን በዓለም አቀፍ ደረጃ ዝነኛ በሆነው ዛሃ ሃዲድ አርክቴክትስ የቀረበ መሆኑን የጠቀሰው ጋዜጠኛው፣ዲዛይኑ የኢትዮጵያን ታላቁ ስምጥ ሸለቆና የተለያየ መልክዓ ምድራዊ ውበትን የሚያንፀባርቅ መሆኑን በጽሁፉ አካቷል። ተጓዦች በአውሮፕላን ማረፊያው ውስጥ ሲዘዋወሩ የኢትዮጵያን ባህልና ተፈጥሮ እንዲመለከቱ በሚያስችል መልኩ የተዘጋጀ ሲሆን፣ለዘላቂነት ቅድሚያ በመስጠት የፀሐይ ብርሃን ኃይልንና የዝናብ ውሃ አሰባሰብ ስርዓትን እንዲጠቀም ተደርጎ ተቀርጿል።   በአጠቃላይ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ መጠናቀቅ፣ኢትዮጵያ በአፍሪካ አቪዬሽን ያላትን መሪነት ከማረጋገጡ ባለፈ የአህጉሪቱን የኢኮኖሚ ትስስር ወደ አዲስ ምዕራፍ እንደሚያሸጋግረው ጋዜጠኛው በሲኤንኤን የጉዞ ገጽ ላይ ባሰፈረው ጽሁፍ ደምድሟል። ይህ ፕሮጀክት ከሌሎች የአፍሪካ አየር መንገዶች ጋር በመተባበር የነጠላ የአፍሪካ አየር ትራንስፖርት ገበያን (SAATM) ወደ ተግባር ለመቀየር የሚደረገውን ጥረት በእጅጉ እንደሚያግዝም ተመልክቷል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ኤክስፖዎች የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የማምረት ዐቅምና የእርስበርስ ትስስር እያጠናከሩ ነው
Apr 23, 2026 103
ድሬዳዋ፤ ሚያዝያ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚዘጋጁ ኤክስፖዎች የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የማምረት ዐቅምና የእርስበርስ ትስስር በማጠናከር ተወዳዳሪነትን ለማላቅ መደላድል እየፈጠሩ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ገለጸ። ድሬ ታምርት፤ ኢትዮጵያ ትበልጽግ በሚል መሪ ሐሳብ በድሬዳዋ የተዘጋጀ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ኤክስፖ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተከፍቷል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በዚሁ ወቅት፤ ኤክስፖዎች የአምራች ኢንዱስትሪዎች የምርት ጥራትና ደረጃን በማሟላት ረገድ የደረሱበትን ከፍታ ለማሳየትና ለሚስተዋሉ ክፍተቶች ዘላቂ መፍትሔ ለመስጠት እያገዙ መሆኑን ተናግረዋል።   በተጨማሪም የእርስበርስ ትስስርን፣ መመጋገብንና ውድድርን በማጠናከር ሀገራዊ ትልምን ከዳር ለማድረስ ምቹ መደላድል እየፈጠሩ መሆኑን አስረድተዋል። ከሚያዝያ 25 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ሀገር አቀፍ ኤክስፖ እንደሚዘጋጅም ጠቁመዋል። በኤክስፖው ላይ ምርታቸውን ያቀረቡ የአምራች ኢንዱስትሪ ተወካዮች በበኩላቸው፤ የግብዓት ልውውጥና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ኤክስፖዎች መዘጋጀታቸው ለአምራች ኢንዱስትሪው ወሳኝ አበርክቶ እንዳላቸው ገልጸዋል። ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎቹ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በተደረገላቸው ድጋፍ ወደ ማምረት የተሸጋገሩ አዳዲስ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ጎብኝተዋል።
አምራች ኢንዱስትሪው ለኢኮኖሚ እድገቱ የሚያበረክተውን ሚና ለማጎልበት ትኩረት ተሰጥቷል
Apr 23, 2026 95
አርባምንጭ፤ ሚያዝያ 15/2018 (ኢዜአ)፡- አምራች ኢንዱስትሪው ለኢኮኖሚ እድገቱ የሚያበረክተውን ሚና ለማጎልበት ትኩረት መሰጠቱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሠ መሥተዳድርና የሥራና ክኅሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሠ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ክልል አቀፍ ኤግዚቢሽንና ባዛር በአርባ ምንጭ ከተማ የተከፈተ ሲሆን፤ የፓናል ውይይትም ተካሂዷል።   አበባየሁ ታደሠ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ አምራች ኢንዱስትሪው ተኪ ምርት ከማምረት አንፃር ያለውን ሚና ለማጉላት በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት አምራች ኢንዱስትሪው ለኢኮኖሚ እድገቱ የሚያበረክተውን ሚና ለማጎልበት ትኩረት መሰጠቱን አረጋግጠዋል።   የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴዔታ ታረቀኝ ቡሉልታ በበኩላቸው፤ አምራች ኢንዱስትሪዎች በሙሉ ዐቅማቸው እንዲያመርቱ የፋይናንስና የኃይል አቅርቦት እንዲሁም የገበያ ችግሮችን ለመፍታት ሁለንተናዊ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የኢንዱስትሪ ልማትን በማፋጠን ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ በመገንባት ጠንካራ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ለመፍጠር በቅንጅት እየተሠራ ነው ያሉት ደግሞ የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሰናይት ሰለሞን ናቸው።   ባለፉት ዘጠኝ ወራትም ከ3 ቢሊየን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ 30 ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቅሰው፤ ለ27 ሺህ 817 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም አስረድተዋል።
ደብረ ብርሀን ከተማ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ማዕከል እየሆነች ነው
Apr 23, 2026 203
ደብረ ብርሃን፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ደብረ ብርሃን ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን የከተማው ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት አስታወቁ። በአትሌት ሻለቃ ሃይሌ ገብረስላሴ በ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር ወጪ በደብረ ብርሃን ከተማ የተገነባው ባለ 4 ኮከብ ዘመናዊ ሆቴል ዛሬ ተመርቋል።   ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው አቶ በድሉ ውብሸት በሆቴሉ ምረቃ ላይ ተገኝተው እንደገለጹት፤ የደብረ ብርሃን ከተማ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ማዕከል እየሆነች መጥታለች።   ዛሬ የተመረቀው ባለ 4 ኮከብ ዘመናዊ ሆቴልም ከተማዋ ታላላቅ አገራዊና ዓለም አቀፋዊ ኮንፈረንሶችን ለማስተናገድ ተመራጭ እንድትሆን የሚያስችላት መሆኑን ገልጸዋል። በተጨማሪም በከተማዋም ሆነ በሰሜን ሸዋ ዞን የሚገኙ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ ቅርሶችን ለመጎብኘት የሚመጡ ቱሪስቶች ቁጥር እንዲጨምር ያግዛል ብለዋል፡፡ ሆቴሉ ለከተማዋ ወጣቶች ተጨማሪ የሥራ ዕድል የሚፈጥርና የከተማዋን ገጽታ የሚገነባ መሆኑን ጠቁመው የከተማ አስተዳደሩ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የሰሜን ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መካሻ ዓለማየሁ በበኩላቸው፤ ሻለቃ ሀይሌ ገብረስላሴ በአትሌትነት ጊዜው "የይቻላል" መንፈስን ለኢትዮጵያውያን ወጣቶች ያስተማረ ጀግና ነው ብለዋል።   በደብረብርሃን ከተማ ያስገነባው ሆቴል ዞኑን የቱሪዝም፣ የኢንዱስትሪና የኮንፈረንስ ማዕከል በማድረግ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የሃይሌ እና ዓለም፤ ዓለም አቀፍ ሆቴሎችና ሪዞርቶች ግሩፕ ባለቤት አትሌት ሻለቃ ሀይሌ ገብረስላሴ እንደገለጸው፤ በሆቴልና ሪዞርት ዘርፍ ኢትዮጵያ ፈጣን እድገት እንድታስመዘግብ የበኩሉን እየተወጣ ነው። ዛሬ በደብረ ብርሃን ከተማ በ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር ተገንብቶ የተመረቀው ባለ 4 ኮከብ ሆቴልም የድርጅቱን የሆቴሎችና ሪዞርቶች ቁጥር ወደ 11 በማሳደግ በዘርፉ ተወዳዳሪ ለመሆን ያስችላል ብሏል።   ሆቴሉ ዓለም አቀፍ ደረጃውን ጠብቆ መገንባቱንና ዘመናዊ የመሰብሰቢያ አዳራሾች፣ የተሟላ ጂምናዚየም እና ልዩ ልዩ አገልግሎቶችን እንዲሰጥ ተደርጎ የተገነባ መሆኑን አብራርቷል። ሆቴሉ በአሁኑ ወቅት ለ200 ዜጎች ቋሚ የሥራ እድል የፈጠረ ሲሆን በሙሉ አቅሙ ወደ ሥራ ሲገባ የሥራ እድል ተጠቃሚዎችን ቁጥር ከ300 በላይ እንደሚሆንም አመልክቷል። በቀጣይም በጎንደር፣ በሐረር እና በድሬዳዋ ከተሞች አዳዲስ መዳረሻዎች በማስገንባት በዘርፉ ተወዳዳሪነቱን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል።
በክልሉ እየተገነቡ ያሉ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ ነው
Apr 23, 2026 115
ጂንካ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል እየተገነቡ ከሚገኙ 11 አነስተኛ ፕሮጀክቶች 7ቱን በተያዘው ዓመት ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በክልሉ ጎፋ ዞን መሎ ኮዛ ወረዳ ቦክሬ ቀበሌ በሚገኘው የቱርሞ ወንዝ ላይ ለሚገነባው አነስተኛ የመስኖ አውታር ግንባታ ፕሮጀክት ከተቋራጩ ጋር የውል ስምምነት ተፈራርሟል።   በፊርማ ስነ-ስርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የቢሮው ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር፣ በክልሉ አርሶና አርብቶ አደር አካባቢዎች 11 አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች እየተገነቡ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በግንባታ ላይ ካሉ 11 ፕሮጀክቶች 7ቱን በዚህ ዓመት እስከ ነሐሴ ወር ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህ ዓመት ከሚጠናቀቁት ፕሮጀክቶች መካከል ብላቴ ኤታ፣ ማርቃላሾ፣ ማዜ፣ ሎማቴ፣ አርጎ፣ ካራዱስ እና ሳላ የተባሉት መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ጭሮ፣ ኩላኖ፣ ሱጋሌ እና ዛሬ የውል ስምምነት የተፈፀመበት የቱርሞ አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክት ደግሞ በሚቀጥለው ዓመት እንደሚጠናቀቁም አስረድተዋል። የቢሮው ምክትል ኃላፊ እና የመስኖ ልማት አስተዳደር ዘርፍ ኃላፊ አቶ ኢሳያስ ቢፍቱ፥ መንግስት በአርሶ እና አርብቶ አደሩ አካባቢ የመስኖ አውታሮችን በማስፋፋት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   በተለይ በቆላማ አካባቢ የሚገኙ ማህበረሰቦችን በመስኖ ልማቱ በማሳተፍ የተጀመረው ልማት ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በቀጣይም አርሶና አርብቶ አደሩን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ በመስኖ ልማቱ ምርታማነታቸውን በእጥፍ የሚያሳድጉበት ሁኔታ ላይ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። ዛሬ የተጀመረው የቱርሞ አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክትም ከ71 ሄክታር በላይ ማልማት የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰው ከ103 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት እንደተመደበለትም ገልጸዋል። ፕሮጀክቱን በ6 ወራት ለማጠናቀቅ ርብርብ እንደሚደረግም ተናግረዋል። የቱርሞ ፕሮጀክት ከአለም ባንክ በተገኘ ብድር በምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም ድጋፍ ከሚተገበሩ የመስኖ ግንባታ ፕሮጀክቶች አንዱ መሆኑንም አንስተዋል።   ግንባታውን የተረከበው በረከት ተሾመ የውሃ ስራዎች ተቋራጭ ባለቤት አቶ በረከት ተሾመ፤ ግንባታውን በፍጥነት፣ በጥራትና በተያዘለት ቀነ ገደብ ለማጠናቀቅ ርብርብ እንደሚደረግ ገልጸዋል። የመስኖ ፕሮጀክቱ የቱርሞ ወንዝን በመገደብ ከከፍታ ቦታ ወደ ዝቅተኛ ቦታ በማፋሰስ ለእርሻ ልማት የማዋል ፅንሰ ሀሳብን የያዘና ይህም ተግባር ነዳጅም ሆነ የኤሌክትሪክ ኃይልን የማይጠቀም በመሆኑ አዋጭ የመስኖ አውታር እንደሆነም ተመልክቷል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በፍራፍሬ ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ሆነዋል
Apr 23, 2026 110
ደብረ ማርቆስ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ባላቸው ፍራፍሬዎች ልማት ሥራ ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጨማሪ ገቢ በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገለጹ። በዞኑ ከ20 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት በቆላና ደጋ የፍራፍሬ ተክሎች እየለማ መሆኑም ተመላክቷል። በምስራቅ ጎጃም ዞን የስናን ወረዳ አርሶ አደር ጌታሁን መንግስቴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ከሰብል ልማት ሥራቸው ጎን ለጎን ከስምንት ዓመት በፊት በትንሽ መሬት ላይ የጀመሩት የአፕል ልማት ሥራቸው ተጠቃሚ እያደረጋቸው ነው። በአሁኑ ወቅት ከሩብ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ልማቱን እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   በየዓመቱ ከሚሰበስቡት የአፕል ምርት እስከ 30 ሺህ ብር ተጨማሪ ገቢ እያገኙ እንደሆነና ቆጥበው ተጨማሪ ሃብት ለማፍራት እንዳገዛቸው ተናግረዋል። ዘንድሮም የአፕል ምርት አያያዙ የተሻለ መሆኑን ገልጸው፣ በምርት ሽያጩ ካለፈው ዓመት የተሻለ ገቢ ለማግኘት ተግተው እየሰሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዞኑ የጎዛምን ወረዳ ነዋሪው አርሶ አደር የሻነህ ጓዴ በበኩላቸው እንዳሉት ከአቮካዶ፣ ማንጎ እና ሎሚ ምርት ሽያጭ በዓመት ከ50 ሺህ ብር በላይ ገቢ እያገኙ ይገኛሉ። ከሰብል ልማት ሥራቸው ጎን ለጎን እያካሄዱት ያለው የፍራፍሬ ልማት ገቢያቸውን ከማሳደጉ ባሻገር ልጆቻቸውን የተመጣጠነ ምግብ ለመመገብና ጤናማ ሆነው እንዲያድጉ እያገዛቸው መሆኑን አስረድተዋል።   በምስራቅ ጎጃም ዞን ግብርና መምሪያ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ባለሙያ ተሾመ በላይ፣ በዞኑ ከ20 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የፍራፍሬ ልማት እየተከናወነና በልማቱም አርሶ አደሮች በመሳተፍ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። ዘንድሮ በዞኑ ከለማው አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ብርቱካን፣ ሎሚ፣ ፓፓያ፣ አፕልና ሌሎች የቆላና የደጋ ፍራፍሬዎች እስካሁን ከ80ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቦ ለገበያ መቅረቡን ጠቁመው፣ በቀሪ ወራትም የበለጠ ምርት ይቀርባል ብለዋል። ከፍራፍሬ ልማት የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ በመጪው የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የሚተከሉ ከ818 ሺህ በላይ የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል። ባለፈው ዓመት በዞኑ ከፍራፍሬ ልማት ከ278ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለገበያ መቅረቡን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
አዲስ ገቢር ነበብ የፖለቲካ ኢኮኖሚ
Apr 23, 2026 529
‎ኢትዮጵያ ቀደም ሲል ከነበረው ግትር ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ አስተሳሰብ ተላቃ፣ ትኩረቱን በተግባራዊ አፈጻጸም ላይ ያደረገ አዲስ ገቢር ነበብ የፖለቲካ ኢኮኖሚ እይታ የተቃኘ የፖሊሲ ማዕቀፍ መከተል ከጀመረች ሰነባብታለች። ‎ይኅው አዲስ አቅጣጫ፤ ሀገሪቱ ለወቅታዊ የዓለምና የሀገር ውስጥ ነባራዊ ሁኔታዎች ምላሽ የሚሰጡ ተግባራዊ መፍትሄዎችን እንድትቀይስ አስችሏታል። በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የሚመራው የሪፎርም ጉዞ፣ መንግሥትንና የግሉን ዘርፍ እንደ ወሳኝ አጋር በማየት፣ በውጤትና በውጤታማነት ላይ የተገነባ አዲስ የመንግሥት የሥራ ባህልን ተቋማዊ አድርጓል። ‎‎በዚህ ገቢር ነበብ እይታ አማካኝነት፣ በሚከተሉት ስምንት ቁልፍ ምሰሶዎች ወሳኝ ስኬቶች ተመዝግበዋል፦ ‎• በኢኮኖሚ ዕይታ ረገድ፦ የመንግሥትን ሚና ዳግም በመተርጎም፣ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያዎችና ዘርፈ-ብዙ የኢኮኖሚ አቅጣጫዎች አማካኝነት የገበያ ውድድር እንዲሰፍንና የኢኮኖሚ አቅም እንዲጎለብት ተደርጓል። ‎• በአማራጭ ፋይናንስ ዘርፍ፦ የካፒታል ገበያ ልማትን በማብሰር፣ የመንግሥትና የግል አጋርነትን በማጠናከር እና ዘመናዊ የገንዘብ ገበያ በመፍጠር የሀገሪቱን የፋይናንስ አማራጮች ማሳደግ ተችሏል። ‎• በኢኮኖሚ አመራር በኩል፦ በመደበኛ ክትትልና ግምገማ፣ በማክሮ ኮሚቴና በዘርፍ ካውንስሎች የተቀናጀ አሰራር አማካኝነት የገንዘብ ፖሊሲና የፕሮጀክቶች አስተዳደር ይበልጥ ውጤታማና ቀልጣፋ እንዲሆን ተደርጓል። ‎• የግል ዘርፍ ሚናን በማሳደግ፦ የግሉ ዘርፍ ከማህበራዊ ኃላፊነት ባለፈ የኢኮኖሚው መሪና ዋና ሞተር እንዲሆን በማድረግ እንደ ትልቅ የልማት አጋር እንዲሳተፍ ምቹ ሁኔታዎች ተፈጥረዋል። ‎• በልማት አጋርነትና ንግድ ትስስር ፦ የብድር ሽግሽግና አዲስ ፋይናንስን በማረጋገጥ፣ ለዓለም ንግድ ድርጅት (WTO) አባልነት የሚደረገውን ሂደት በማፋጠንና የAfCFTA ትግበራን ውጤታማ በማድረግ የሀገሪቱ ዓለም አቀፋዊ የንግድ ተወዳዳሪነት ከፍ ብሏል። ‎• በማህበራዊ ደህንነት ረገድ፦ አካታችነትን፣ ተደራሽነትንና ጥራትን መሠረት ያደረገ የሰው ተኮር ድጋፍ ሥርዓት በመዘርጋት፣ የማህበራዊ ጥበቃ አገልግሎቶች ዘላቂነት እንዲኖራቸው ማድረግ ተችሏል። ‎• በፍትሃዊ የመሰረተ ልማት ስርዓት ፦ የአካባቢ ጸጋን መሠረት ያደረገ፣ በግልጽ የሕግ ማዕቀፍ የሚመራና ያለፉ የፍትሃዊነት ክፍተቶችን የሚሞላ የመሰረተ ልማት ግንባታ ሥርዓት ተግባራዊ ሆኗል። ‎• በስርዓት ግንባታ በኩል፦ ብሔራዊ አካታች ምክክርን በማካሄድ፣ በፍትህና በሲቪል ሰርቪስ ዘርፎች ሪፎርም በማድረግ እንዲሁም የዲሞክራሲ ተቋማትን በማጠናከር ረገድ ጉልህ ውጤቶች ተመዝግበዋል። #PMOEthiopia
ኮርፖሬሽኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 35 ባለሀብቶችን ወደ ስራ አስገብቷል
Apr 23, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ የኦሮሚያ ክልል ኢንዱስትሪ ልማት ፓርኮች ኮርፖሬሽን በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት 35 ባለሀብቶችን ተቀብሎ ወደ ስራ ማስገባት መቻሉን ገለጸ። ኮርፖሬሽኑ በተለይ የገቢ ምርቶችን በሚተኩ የልማት ዘርፎች ላይ ትኩረት አድርጎ በመስራቱም ውጤታማ ጅምር መኖሩን አረጋግጧል። በኮርፖሬሽኑ የልማት ዘርፍ ምክትል ስራ አስፈጻሚ አቶ ሰለሞን ቱፋ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኮርፖሬሽኑ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን የማልማት ፣ የማስተዳደርና ገቢ የማመንጨት ተልዕኮውን በስኬት እየተወጣ ይገኛል። በበጀት ዓመቱም ባለሀብቶች በቡልቡላ የተቀናጀ ኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ በመካከለኛ ኢንዱስትሪ ማዕከላት፣ ጥቃቅን ኢንዱስትሪ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ገቢን ለማመንጨትና ተኪ ምርቶችን ለማምረት ወደ ስራ መግባታቸውንም ነው የገለጹት።   ባለሀብቶቹ በዋናነት በምግብ ዘይት፣ በጥራጥሬና ፍራፍሬ ልማት እንዲሁም በተለያዩ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፎች ላይ መሰማራታቸውን ተናግረዋል። ባለሀብቶቹ ስራ የጀመሩት መሰረተ ልማት በተሟላላቸው ስፍራዎች መሆኑን የገለጹት አቶ ሰለሞን፣ በዋናነትም የቡልቡላ የተቀናጀ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ እና በስሩ የሚገኙ 6 መካከለኛ ኢንዱስትሪ ማዕከላት መሆናቸውን ጠቁመዋል። በበጀት ዓመቱም 35 ባለሀብቶችን ወደ ማምረት ስራ ማስገባት በመቻሉ በአጠቃላይ የአልሚ ባለሀብቶች ቁጥር 81 ደርሷል ብለዋል። በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት 3 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሊትር የምግብ ዘይት በኮርፖሬሽኑ ስር በሚገኙ ፓርኮች ተመርቶ ለገበያ የቀረበ ሲሆን፣ ከዚህም 1 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ገቢ ተገኝቷል ብለዋል።   ወደ ስራ በገቡት አምራች ኢንዱስትሪዎች 3 ሺህ 225 ዜጎች የስራ ዕድል ማግኘታቸውንም አስታውቀዋል። በነቀምቴ የተቀናጀ ኢንዱስትሪ ፓርክ ከለማው 60 ሄክታር መሬት ውስጥ 10 ሄክታሩ ለባለሀብቶች የተላለፈ ሲሆን ከተገነቡት ሶስት ሼዶች መካከል ሁለቱ ለባለሀብቶች እንዲተላለፉ መደረጉንም ገልፀዋል። ኮርፖሬሽኑ በቀጣይም የለሙ መሬቶችን በማቅረብና አምራቾች ምርቶቻቸውን በስፋት ለገበያ እንዲያቀርቡ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ምክትል ስራ አስፈጻሚው አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ታምርት የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ሚያዝያ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል
Apr 23, 2026 80
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ሚያዝያ 18 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ይካሄዳል፡፡ የጎዳና ላይ ሩጫውን በተመለከተ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል። የ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ታምርት የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ አስተባባሪ አብዱልፈታህ የሱፍ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ ታምርት የአስር ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ ሚያዝያ 18 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ይካሄዳል። የሩጫ ውድድሩ ገቢ ምርትን በመተካት የተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች የስፖርት አልባሳትን ማስተዋወቅ እና የማምረት አቅማቸውን ማሳየትን አላማ ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ዜጎች የሀገር ውስጥ ምርትን የመጠቀም ባህል እንዲያሳድጉ ግንዛቤ የሚፈጠርበት መሆኑንም አመላክተዋል። ውድድሩ አዲስ አበባ ከተማ ያላትን የቱሪዝም ሀብት ለማስተዋወቅ ተጨማሪ እድል እንደሚፈጥርም እንዲሁ። በውድድሩ ከ15 ሺህ በላይ ተሳታፊዎች እንደሚገኙ እና ከእነዚህ ውስጥ 500 የሚሆኑት አትሌቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህ ውድድር በሴቶችና በወንዶች 1ኛ ለሚወጡ 550 ሺህ ብር፣ 2ኛ ደረጃን ለሚይዙ 300 ሺህ ብር እንዲሁም በ3ኛነት ለሚያጠናቅቁ ደግሞ 200 ሺህ ብር እንደሚበረከት ተናግረዋል። በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የተሳትፎና ውድድር ዳይሬክቶሬት ተወካይ ጊዜ አድነው በበኩላቸው፤ የጎዳና ላይ ሩጫው ለአትሌቶች አዲስ የውድድር እድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል።
በክልሉ ከ2 ሺህ 800 በላይ ትራክተሮችን በማሰማራት ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
Apr 23, 2026 86
ባህርዳር ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በቀጣዩ የመኸር ወቅት ከ2 ሺህ 800 በላይ ትራክተሮችን በማሰማራትና በሜካናይዜሽን እርሻ ተጨማሪ ምርት በማምረት ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ትኩረት መደረጉ ተገለፀ። በክልሉ ግብርና ቢሮ የግብርና ግብዓትና የገጠር ፋይናንስ አቅርቦት ዳይሬክተር ወይዘሮ ሙሽራ ሲሳይ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ የክልሉ አርሶ አደር የምግብ ዋስትናውን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት እንዲያመርት እየተሰራ ነው።   በኩታ ገጠም በማልማት፣ የሜካናይዜሽን አሰራርን በመከተል፣ ግብዓትንና ሌሎች ቴክኖሎጂዎችን በአግባቡ በመጠቀም የምርት ጭማሪውን ለማሳካት ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ‎‎በዚህም በአርሶ አደሩና በባለሃብቱ እጅ የሚገኙ ከ2 ሺህ 800 በላይ የእርሻ ትራክተሮችን በማሰማራት 1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በሜካናይዜሽን ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን አስረድተዋል። ከዚህ ውስጥም 683 የእርሻ ትራክተሮችና 12 ኮምባይነሮች በያዝነው በጀት ዓመት የተሰራጩ በመሆኑ ምን ያህል ለዘርፉ ትኩረት እንደተሰጠ ማሳያ ነው ብለዋል። ‎በተጨማሪም ‎የምርት ብክነትን ለመቀነስም ከወዲሁ ከአንድ ሺህ በላይ አነስተኛ የሰብል መውቂያና የበቆሎ መፈልፈያ ማሽኖችን ለአርሶ አደሮች ተደራሽ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። አሁን እየጣለ የሚገኘው ዝናብም ለእርሻ ስራ አመቺ በመሆኑ አርሶ አደሩ በቴክኖሎጂ ታግዞ የእርሻ ስራውን ከወዲሁ አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አሳስበዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የወንበርማ ወረዳ አርሶ አደር ባዩ ተጃረ ፤ በበቆሎና ስንዴ ሰብል የሚያለሙትን ሁለት ሄክታር መሬት በትራክተር ለማረስ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።   ዘንድሮ ቀድሞ መጣል የጀመረው ዝናብ የእርሻ ስራ ለማከናወን ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ጠቁመው መሬቱን ቀድሞ በማለስለስ በወቅቱ ለመዝራት መዘጋጀታቸውን አስረድተዋል። በትራክተር ማረስ የሚያስገኘውን ጥቅም በመገንዘብ ከሁለት ሄክታር በላይ ማሳቸውን በሜካናይዜሽን ለማልማት መዘጋጀታቸውን የገለጹት ደግሞ የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ተመስገን ታደለ ናቸው። ይህም የአርሶ አደሩን ጊዜና ጉልበት ከመቆጠብ በተጨማሪ ለሰብል ምርታማነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑን አስረድተዋል።  
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥና የራስን አቅም የመገንባት ታሪካዊ ጉዞ ነው 
Apr 23, 2026 221
ድሬዳዋ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የሀገርን የኢኮኖሚ ነፃነት በማረጋገጥ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር ታሪካዊ ጉዞ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል ገለጹ። ሚኒስትሩ መላኩ አለበል ይህን የተናገሩት "ድሬ ታምርት ኢትዮጵያ ትበልፅግ" በሚል መሪ ሃሳብ በተዘጋጀው የአምራች ኢንዱስትሪዎች ኤክስፖ የፓናል ውይይት ላይ ነው።   አቶ መላኩ በወቅቱም፤ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች ዘርፍ በተደረገው ድጋፍና ክትትል እመርታዊ ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል። በንቅናቄው የተዘጉ አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ እንዲመለሱ በማድረግ ከውጭ የሚገቡ ምርቶች በጥራትና በስፋት እየተተኩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በማምረት፣ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶችን በመሳብ እና የስራ ዕድል በመፍጠር ረገድም መሠረታዊ ውጤቶች መገኘታቸውን በመጥቀስ። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የሀገርን የኢኮኖሚ ነፃነት በማረጋገጥ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር ታሪካዊ ጉዞ መሆኑን በአፅንኦት ገልጸዋል። በሌሎች ሀገራት አልባሳት፣ መድኃኒት፣ መገልገያዎችና ሌሎች ምርቶች ላይ ጥገኛ የሆነ አገር ሉዓላዊነቱን ማረጋገጥ እንደማይችል በማመላከት። በንቅናቄው በተሰሩ ስራዎች በዘንድሮ በጀት ዓመት ብቻ 13 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ያስመዘገቡ የውጭ ሀገራት ባለሃብቶች ወደ ኢትዮጵያ ገብተው በዘርፉ ለመሰማራት መዘጋጀታቸውን አስታውሰዋል። ዘርፉን ይበልጥ ለማሳደግና በኢኮኖሚው ውስጥ የመሪነት ድርሻውን እንዲያረጋግጥ የህግና የፖሊሲ ማሻሻያዎች እየተደረጉ ይገኛሉም ብለዋል።   የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች በተደረጉ ድጋፎች ተዘግተው የነበሩ 15 ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ወደ ማምረት በማሸጋገር ከ9 ሺህ 200 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች ቋሚ የስራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል። አምራች ኢንዱስትሪዎቹ ተኪ እና ወጪ ምርቶችን በስፋትና በጥራት እያመረቱ መሆኑን ጠቅሰው ከንቅናቄው በኋላ የኢንዱስትሪዎቹ የማምረት አቅም ከ42 በመቶ ወደ ወደ 64 በመቶ ከፍ ማለቱን አንስተዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሀርቢ ቡህ፤ ባለፉት አራት ዓመታት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የተሰሩ ስራዎች ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ማስቻላቸውን ገልፀዋል።   በተደረጉ ሁሉን አቀፍ ድጋፎችና ክትትሎች የተዘጉ እና በግንባታ ላይ ያሉ ፋብሪካዎች ወደ ማምረት መሸጋገራቸውን በማስታወስ። ባለፉት ዓመታት 253 ቢሊዮን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ ከ2 ሺህ 620 በላይ ባለሃብቶች ፍቃድ ወስደው ወደ ዘርፉ መግባታቸውን ጠቅሰው ወደ ማምረት የተሸጋገሩትም ከ10ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ፈጥረዋል ብለዋል። በፓናል ውይይቱ ላይ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴርና የድሬዳዋ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች፣ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ባለቤቶች፣ የኃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ተሳታፊ ሆነዋል።
የደዋጨፋ ወረዳ አርሶ አደሮች ቋሚ የሆኑ የፍራፍሬ ተክሎችን ለማልማት የችግኝ ተከላ ስራ ጀምረዋል
Apr 23, 2026 79
ደሴ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦ቋሚ የሆኑ የፍራፍሬ ተክሎችን ለማልማት የችግኝ ተከላ ስራ መጀመራቸውን በኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን የደዋጨፋ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ። የዞኑ አስተዳደር በበኩሉ ከሁለት ሺህ 300 ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም የፍራፍሬ ልማት ማረስ መጀመሩን አስታውቋል። በዞኑ በደዋጨፋ ወረዳ የሸክላ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መሀመድ ሁሴን ለኢዜአ እንደገለጹት፣ አንድ ሄክታር ማሳቸውን በኩታ ገጠም በሙዝ ተክል በማልማት የተሻለ ተጠቃሚ ለመሆን እየሰሩ ነው።   እስካሁን ከ800 በላይ የተሻሻሉ የሙዝ ችግኞችን መትከላቸውን ጠቁመው፣ ችግኞቹ ጸድቀው ተገቢውን ምርት መስጠት እንዲችሉ እንክብካቤ እያደረጉ እንደሚገኙ አስረድተዋል። በአካባቢው ዓመቱን ሙሉ የሚፈስ ወንዝ ቢኖርም እስካሁን እንዳልተጠቀሙበት ጠቁመው የተከሉት የሙዝ ችግኝ በዘጠኝ ወር ምርት የሚሰጥ በመሆኑ ተጠቃሚነታችንን የሚያረጋግጥ እንደሚሆንም እምነት አለኝ ብለዋል። ሌላው የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ ወጣት እንድሪስ ሁሴን በበኩሉ፤በሁለት ሔክታር መሬት ላይ መንግስት በነጻ ያቀረበላቸውን የተሻሻለ የፍራፍሬ ችግኝ በኩታ ገጠም እርሻ ማሳቸው እያለሙ እንደሚገኙ ተናግሯል።   ከፍራፍሬ ተክሎቹ ውስጥ ሙዝና ፓፓያን እያለማ ሲሆን እስካሁን አንድ ሺህ 600 የሙዝ ችግኞችን ለመትከል ችያለሁ ነው ያለው። በአካባቢው ቀድመው በፍራፍሬ ልማት ስራ ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ መሆናቸውን በማየት ወደ ሙዝ ልማቱ መግባታቸውን ገልጿል። ግማሽ ሄክታር ማሳዬን በፍራፍሬ ለማልማት የሙዝ ችግኞችን መትከል ጀምሪያለሁ ያሉት ደግሞ በወረዳው የገርቢ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አህመድ ኡመር ናቸው።   መንግስት በአጭር ጊዜ ምርት የሚሰጥ፣ ምርታማና በሽታን የሚከላከል የሙዝ ዝርያ በነጻ ያቀረበልን በመሆኑ ተገቢውን እንክብካቤ አድርገን የተሻለ ተጠቃሚ ለመሆን እየሰራን ነው ብለዋል። የኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አህመድ አሊ በበኩላቸው፣ በዞኑ ፍራፍሬ በስፋት በማልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ከሁለት ሺህ 300 ሄክታር በላይ መሬት በኩታገጠም እርሻ ፍራፍሬን የማልማት ሥራ መጀመሩንም ነው ያስረዱት። ልማቱን ለማሳለጥም ለአርሶ አደሩ በአጭር ጊዜ ምርት የሚሰጥ፣ በሽታን የሚከላከልና ምርታማ የሆኑ የሙዝ ችግኝ በነጻ ማቅረብ መቻሉን አመላክተዋል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን በማዕድን ዘርፍ ለወጣቶች የስራ ዕድል በመፍጠር ተጠቃሚነታቸውን ማሳደግ ተችሏል
Apr 23, 2026 67
ገንዳውኃ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦በምዕራብ ጎንደር ዞን በለውጡ መንግስት ልዩ ትኩረት በተሰጠው የማዕድን ዘርፍ ለወጣቶች የስራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚነታቸውን ማሳደግ መቻሉ ተገለጸ። ​የዞኑ ማዕድን ሀብት መምሪያ ኃላፊ ተወካይና የማዕድን ሥራዎች ፈቃድ አስተዳደር ባለሙያ አቶ ወረቀት ቆየ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ዞኑ እምቅ የማዕድንና ግብርና ኢንቨስትመንት ሃብት ያለው ነው።   በዚህም በዞኑ ባለፉት 9 ወራት ያለውን ማእድን ለማልማት በተደረገ ጥረት በ32 ማህበራት ለተደራጁ ከ470 በላይ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልጸዋል። የስራ ዕድሉን መፍጠር የተቻለውም በኦፓል፣ በጥቁር ድንጋይና በነጭ አሸዋ ማውጣት መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ በተደጋጋሚ በተጠናው ጥናት መሰረት የወርቅ፣ የብረት፣ የኦፓል፣ የጄሶ፣ የሲልካ፣ የመዳብና የኒኬል ማዕድናት በስፋት እንደሚገኙ መረጋገጡን አስረድተዋል።   በቀጣይ ከክልሉ ጋር በመነጋገርና ባለሃብቶችን ወደ አካባቢው በመሳብ የማዕድን ሃብቱን በማልማት ተጨማሪ የስራ እድል ለመፍጠር በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል። ከማዕድን ልማቱም ገቢ በመሰብሰብ ለልማት ማዋል መቻሉን ጠቁመው የመጣውን ሰላም በመጠቀም በቀጣይ የስራ እድል ፈጠራውን ለማሳደግ ይሰራል ብለዋል። ​በገንዳውሃ አካባቢ በአሽዋና በድንጋይ ማዕድን ልማት ስራ ላይ በመደራጀት ወደ ስራ ከገቡ ወጣቶች መካከል ወጣት ዮሴፍ ዳኘ እንደገለጸው፤ በከተማዋ ለሚካሄደው የኮሪደር ልማት ግብዓት በማቅረብ ውጤታማ ሆነዋል። በባህላዊ መንገድ ማዕድን በማውጣት ዘርፍ ላይ የተሰማሩት አቶ ምህረት ደጀኔ በበኩላቸው፤ በመንግሥት በኩል እየተደረገላቸው ያለው ድጋፍ የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ ህገ-ወጥ የማዕድን ዝውውርን በመከላከልና የተደራጁ ዜጎች ሰርተው እንዲለወጡ እየተደረገ ያለው ጥረት ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አመልክተዋል።
ተሻሽሎ የፀደቀው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ የሀገራችንን የአየር ትራንስፖርት ዕድገት አንድ ደረጃ ከፍ ያደርገዋል
Apr 22, 2026 811
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2018(ኢዜአ)፦ ተሻሽሎ የፀደቀው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ የሀገራችንን የአየር ትራንስፖርት ዕድገት አንድ ደረጃ ከፍ እንደሚያደርገው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ገለጸ። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው 15ኛ መደበኛ ስብሰባ የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅን ለማሻሻል የቀረበውን ረቂቅ አዋጅ 1412/18 መርምሮ አጽድቋል፡፡ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ በላከው መረጃ እንዳመለከተው፤ ከ21 ዓመታት በኋላ ተሻሽሎ የፀደቀው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ ተቋሙ የአቪዬሽን ደኅንነት ሥራዎችን በበላይነት ለመምራት እና ለማስተባበር የተሰጠውን ሀገራዊ ተልዕኮ ከስያሜው አንስቶ በግልፅ ያካተተ ሲሆን፤ የሀገራችንን የአየር ትራንስፖርት ዕድገት አንድ ደረጃ ከፍ ለማድረግ ያግዛል፡፡   የአቪዬሽን ደኅንነትን ለማጠናከር ትኩረት ከሚሰጣቸው ጉዳዮች ውስጥ የመጀመሪያው የሕግ ማዕቀፍ መሆኑንም አገልግሎቱ በመረጃው አመላክቷል። በዚህ ረገድ ነባሩ አዋጅ ኢንዱስትሪውን በሚፈለገው ደረጃ ለማሳደግ ተግዳሮት ሆኖ ከመቆየቱም በላይ የዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት (ICAO) ተቀጽላ 17 ስታንዳርዶችን ሳያካትት መቆየቱንም ጠቁሟል፡፡ ተሻሽሎ የፀደቀው አዋጅ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የተሰጠውን የአቪዬሽን ደኅንነትን የማረጋገጥ ሀገራዊ ተልዕኮ በላቀ ብቃት ከመወጣት አንፃር የጥራትና የቁጥጥር ስራዎች ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን ጠብቀው እንዲከናወኑ የሚያስችሉ ሕጎችን መያዙም ተመላክቷል፡፡ አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ በአቪዬሽን ደኅንነት ረገድ ላስቀመጠው ራዕይ እና ስትራቴጂክ ግብ ስኬት መሰረት የሚጥል መሆኑም ጠቅሷል፡፡   ከቴክኖሎጂ አንፃር ኢንዱስትሪውን ለማዘመን አስፈላጊ የሆኑ ባለድርሻ አካላትን በኮሚቴነት መጨመሩ፤ የዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት ስታንዳርዶችን በአዲስ መልክ ማካተቱ፤ የአየር መንገዱን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ እገዛ የሚያደርግ መሆኑና ከኢንዱስትሪው ፈጣን እድገት ጎን ለጎን ለመጓዝ አቅም መፍጠር የሚያስችል የሕግ ድጋፍ መስጠቱ በፋይዳነት የሚጠቀሱ መሆናቸውንም በመረጃው ተገልጿል፡፡ የተሻሻለው የኢትዮጵያ አቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አዋጅ ቁጥር 1412/18 በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሚያዝያ 13 ቀን 2018 ዓ.ም በአብላጫ ድምጽ መጽደቁንም አገልግሎቱ በመረጃው አመልክቷል፡፡
በተተገበሩ የሪፎርም ስራዎች የግብርና ዘርፉን ወደ ሜካናይዜሽን ማሸጋገር ያስቻሉ ተጨባጭ ወጤቶች ተመዝግበዋል
Apr 22, 2026 573
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት የለውጥ ዓመታት በኢትዮጵያ የተተገበሩ የሪፎርም ስራዎች የግብርና ዘርፉን ወደ ሜካናይዜሽን ማሸጋገር ያስቻሉ ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ። የ2018 በጀት ዓመት ሦስተኛው የመቶ ቀናት እና የዘጠኝ ወራት ስራ አፈጻጸም ሪፖርት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ተገምግሟል። የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ በሰጡት ማብራሪያ፣ በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የተተገበሩ የሪፎርም ስራዎች የግብርና ዘርፉን ወደ ሜካናይዜሽን ማሸጋገር የሚያስችሉ ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውን ገልፀዋል። በዚህም አጠቃላይ ኢኮኖሚው ወደ ፊት እንዲራመድ፣ ፈጣንንና ጥራት ያለው ኢኮኖሚ እንዲመዘገብ በማስቻል ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደርግ እድገት መመዝገቡን ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደም ዝቅተኛ የግብርና ማሽነሪ ቁጥር ለማሳደግ መንግሥት የፖሊሲ ማበረታቻ በማድረግ አርሶ አደሮቹ ማሽነሪዎችን ከቀረጥ ነፃ እንዲያስገቡ እና የብድር አቅርቦት በማመቻቸት ሰፊ ስራ መሰራቱን አንስተዋል። በዚህም ባለፉት የለውጥ ዓመታት በተሰራው ስራ ወደ 27 ሺህ ትራክተሮች ከ8 ሺህ በላይ ኮምባይነሮች እንዲሁም ከ280 ሺህ በላይ በሞተር የሚሰሩ ፓምፖች ተደራሽ ማድርግ መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም የግብርናው ስራ ከዝማላዳዊ አሰራር ተላቆ ወደ ሜካናይዜሽን እየተሸጋገረ መሆኑን ጠቅሰው፤ ባለፉት አመታት በተሰራ ስራ የሜካናይዜሽን እድገቱ 72 በመቶ መድረሱን ያሳያል ነው ያሉት። አጠቃላይ በኢትዮጵያ በትራክተር የሚለማ መሬት 7 ሚሊየን ሄክታር መሬት የደረሰ ሲሆን ይህ ማለት ከሚለማው መሬት አንድ ሶስተኛውን በትራክተር ማልማት እንደተቻለ ገልፀዋል። ይህም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ለገበያ የሚቀርበውን ምርት በማሳደግ የአርሶ አደሩን ህይወት በመቀየር ረገድ ትልቅ ለውጥ ማስመዝገቡን ጠቁመዋል። በመሆኑም ባለፉት የለውጥ አመታት ተግባራዊ የተደረገው ሪፎርም የግብርና ትራንስፎርሜሽንን ለማረጋገጥ ትልቅ አቅም የፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ግብርናውን ከዝናብ ጥገኝነት ወደ መስኖ ለማሸጋገር በተደረገው ጥረት የመስኖ ልማት ሽፋኑ ከዓመት ወደ ዓመት እየጨመረ መጥቷል ነው ያሉት። በዘንድሮው ዓመት ብቻ 4 ነጥብ 2 ሚሊየን ሄክታር መሬት በመስኖ ስንዴ ለማልማት ታቅዶ እስካሁን ወደ 3 ነጥብ 87 ሚሊየን ሄክታር ማልማት መቻሉን ጠቅሰዋል። ይህም አርሶ አደሩ ከዝናብ ጥገኝነት በመላቀቅ በዓመት ሁለትና ከዚያ በላይ እንዲያመርት በማድረግ እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ተጨባጭ ለውጥ ማሳየቱን ተናግረዋል። በተጨማሪም ለዜጎች ሰፋፊ የስራ እድል እየፈጠረ እንደሚገኝም ገልጸዋል። አርሶ አደሩ ከምግብነት ባለፈ በመጠንም በጥራትም ተወዳዳሪ ምርቶችን በማምረት ለዓለም ገበያ ተደራሽ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ወራት 4 ነጥብ 85 ቢሊየን ዶላር የሚያወጡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካት ተችሏል
Apr 22, 2026 543
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ 4 ነጥብ 85 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጡ ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካት መቻሉን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለዘርፉ ትልቅ መሰረት መጣሉን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ በገጠር ኢንዱስትሪያላይዜሽን 754 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት መግባታቸውን ጠቁመዋል። የ2018 በጀት ዓመት ሦስተኛው የመቶ ቀናት እና የዘጠኝ ወራት ስራ አፈጻጸም ሪፖርት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ተገምግሟል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በሰጡት ማብራሪያ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግርን በማሳካት ረገድ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል። የሪፎርም ሥራዎቹ ምርትና ምርታማነትን በመጨመር እንዲሁም የዜጎችን ኑሮ በማሻሻል ስኬታማ መሆናቸውን አንስተዋል። ቀደም ሲል 4 ነጥብ 8 በመቶ ብቻ የነበረው የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ዕድገት አሁን ላይ በሁለት አሃዝ አድጎ ከ13 በመቶ በላይ ደርሷል ነው ያሉት። የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሀብቶች ገቢ ምርትን በመተካትና በወጪ ንግድ ዘርፍ አመርቂ ለውጥ ማምጣታቸውን ጠቁመዋል። ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ 433 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጡ የኢንዱስትሪ ምርቶች ለውጭ ገበያ የቀረቡ ሲሆን የዘርፉ የኃይል አጠቃቀምም ማደጉን ተናግረዋል። የገቢ ምርትን በሀገር ውስጥ ለመተካት በተሠራው ሥራ 4 ነጥብ 85 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጡ ተኪ ምርቶችን ማምረት መቻሉን አስታውቀዋል። ይህ ውጤት የኑሮ ጫናን በማቅለል እና የኢኮኖሚ መነቃቃትን በማምጣት ረገድ ትልቅ ሚና መጫወቱን አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለዘርፉ ትልቅ መሰረት መጣሉን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ በገጠር ኢንዱስትሪያላይዜሽን 754 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት መግባታቸውን ጠቁመዋል። በቀጣይም የምርት አቅምን ለማሳደግ የፋይናንስ፣ የግብዓት፣ የኃይል አቅርቦት እና ምቹ የገበያ ሁኔታዎችን በመፍጠር ላይ በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከማዕድን ዘርፍ ወጪ ንግድ አራት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ ተገኝቷል
Apr 22, 2026 375
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከማዕድን ዘርፍ ኤክስፖርት አራት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ መገኘቱን የማዕድን ሚኒስትር ኢንጅነር ሀብታሙ ተገኝ ገለጹ፡፡ የ2018 በጀት ዓመት ሦስተኛው የመቶ ቀናት እና የዘጠኝ ወራት ስራ አፈጻጸም ሪፖርት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ተገምግሟል። የማዕድን ሚኒስትሩ ኢንጅነር ሀብታሙ ተገኝ በሰጡት ማብራሪያ፣ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ ከማዕድን ወጪ ንግድ ወደ አራት ቢሊዮን ዶላር ገደማ ገቢ መገኘቱን ይፋ አድርገዋል። እንደ ሚኒስትሩ ማብራሪያ፣ በዘርፉ የታየው ውጤት ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ87 በመቶ እድገት አሳይቷል። ይህ የአራት ቢሊዮን ዶላር ገቢ ከሦስት ዓመታት በፊት የሀገሪቱ አጠቃላይ ዓመታዊ የኤክስፖርት ገቢ የነበረውን ያህል መሆኑ፣ ዘርፉ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያመጣውን ግዙፍ ለውጥ ያመላክታል ብለዋል። ለዘርፉ ስኬት ዋነኛው ምክንያት የሀገሪቱ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ማሻሻያ መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይም ባለሀብቶች ያገኙትን ትርፍ በውጭ ምንዛሬ ወደ ውጭ ማውጣት መቻላቸው፤ የኢንቨስትመንት ስጋቶች መቀነሳቸው እና መንግሥት ለዘርፉ የሰጠው ልዩ የማበረታቻ ሥርዓት በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቁ ግዙፍ ኩባንያዎች ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጡ አድርጓል ነው ያሉት። ከወርቅ ባለፈ ሌሎች ማዕድናትም ትኩረት እንደተሰጣቸው አንስተዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ከፍተኛ የወርቅ ሀብት ካላቸው ሀገራት ተርታ እየተሰለፈች ሲሆን፥ ከወርቅ በተጨማሪ ሌሎች ማዕድናት ላይ ትኩረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በፍለጋ ደረጃ የነበሩ እንደ ጋዝ፣ ፖታሽ፣ ሊቲየም እና ኒኬል ያሉ ማዕድናት ወደ ምርት እንዲገቡ እየተደረገ መሆኑን ነው ያነሱት። እነዚህ ማዕድናት በቀጣይ የዘርፉን የኤክስፖርት ገቢ በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያሳድጉትም አንስተዋል። ከማዕድን ወጪ ንግድ ባሻገር እንደ ብረት፣ ሲሚንቶ እና ድንጋይ ከሰል ያሉ ማዕድናት የሀገር ውስጥ ፍላጎትን በማሟላት የውጭ ምንዛሬን ለማዳን ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ ነው ያሉት። ከሀገር ውስጥ ፍላጎት የሚተርፈው ምርት ደግሞ ወደ ውጭ ገበያ እንደሚላክ አስረድተዋል። አዲስ የተረቀቀው የማዕድን ፖሊሲ ሲጸድቅ እና አሁን የተጀመረው የሪፎርም ስራ ተጠናክሮ ሲቀጥል፣ ዘርፉ ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ይበልጥ እንደሚያድግ አብራርተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም