ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ረቂቅ አዋጁ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮችን ወደ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ እና ገበያ መር ሥርዓት ለማሸጋገር ጉልህ አስተዋጽኦ ይኖረዋል
Jun 10, 2026 847
አዲስ አበባ፤ሰኔ 3/2018 (ኢዜአ)፦የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮችን ወደ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ እና ገበያ መር ሥርዓት ለማሸጋገር ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የፖለሲና የምግብ ስርዓትና ጥናት ሲኒየር ዳይሬክተር ረታ ዋጋሪ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አምራቾች በኩባንያ በማደራጀት፣ መሬት የመጠቀም መብታቸውን፣ የእንስሳት ሀብታቸውንና ጉልበታቸውን ወደ ካፒታል በመለወጥ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የሚያስችል ግልጽ የሕግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ ረቂቅ አዋጁ መዘጋጀቱን አብራርተዋል። ረቂቅ አዋጁ በርካታ ዓላማዎች ያካተተ መሆኑን የጠቀሱት ዳይሬክተሩ ለዘርፉ ዕድገት ምቹ የሆነ ግልጽ አሠራር መዘርጋት፣ አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አምራቾች ወደ መካከለኛ አልሚነት በመሻገር ኑሮአቸውን እንዲያሻሽሉ ማስቻል እንዲሁም ለገጠር ትራንስፎርሜሽን እውን መሆን የጎላ አስተዋጽኦ ማድረግ የሚሉ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡ አዋጁ ለአነስተኛ ይዞታ አምራቾች የፋይናንስ እና የኢንሹራንስ ተደራሽነትን በማመቻቸት፣ ከዘመናዊ አሠራርና አገልግሎቶች ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የግብርና ቢዝነስ ኩባንያዎች የማቋቋሚያ ካፒታል፣ የአባላት ምዝገባ ፣ የኩባንያዎች አደረጃጀት ፣ የተቋማት ስልጣንና ተግባር የሕግ ተጠያቂነትና ሌሎች ጥያቄዎች ከቋሚ ኮሚቴው አባላት ተነስተዋል። በግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት አማካሪ አቶ ሽመክት ማሩ በሰጡት ማብራሪያ፤ በረቂቅ አዋጁ ላይ የተቀመጡት የኩባንያዎች መሥራች አባላት ቁጥር እና የማቋቋሚያ መነሻ ካፒታል መስፈርቶች መካተታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ መስፈርቶቹ ባለፉት ዓመታት በሀገሪቱ የግብርና ዘርፍ ከተገኙ ልምዶች፣ ከዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችና ጥልቅ ጥናቶች ላይ ተመስርተው የተቀረጹ መሆናቸውን አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሤ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ የተዘጋጀበት ዋና ዓላማ የግብርና ግብዓትና ቴክኖሎጂ አቅርቦትን በማሳለጥና ተደራሽ በማድረግ የአነስተኛ ይዞታ አምራቾችን ምርት፣ ምርታማነትና ገቢ ለማሳደግ መሆኑን አንስተዋል። አዋጁ የግብርና ምርትን በከፍተኛ መጠንና ጥራት በማሰባሰብ፣ የግብይትና የእሴት ጭመራ ተግባራትን በማዘመን ረገድ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ይህ መሆኑ የአነስተኛ ይዞታ አምራቾችን የኑሮ ደረጃ ከማሻሻሉም በላይ ለሀገሪቱ አጠቃላይ ኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ያሰችላቸዋል ብለዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ፤ ረቂቅ አዋጁ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮችን በግብርና ቢዝነስ ኩባንያ በማደራጀትና በማቀናጀት፣ ምርታማነትን ለማጎልበትና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡ አዋጁ በግብርናው ዘርፍ የእሴት ጭመራን ለማምጣት እንዲሁም ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በማሳደግ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማጎልበት እንደሚያስችል ጠቅሰዋል።
የታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የታክስ አሰራርን በማዘመን ፍትሐዊነትና የሕግ ተገዢነትን ለማረጋገጥ እገዛ ያደርጋል
Jun 10, 2026 759
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2018 (ኢዜአ)፡- የታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የታክስ አሰራርን በማዘመን ፍትሐዊነትና የሕግ ተገዢነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር የአስረጂ መድረክ ተካሂዷል። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ፍቃዱ ሆረታ በዚህ ወቅት፤ የታክስ አስተዳደር ረቂቅ አዋጅ ከኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ጋር የተጣጣመ ዘመናዊ የታክስ አሰራር ለመፍጠር ያስቻላል ብለዋል። በታክስ ከፋዩ ማህበረሰቡ የሚነሱ መሰረታዊ የፍትሐዊና የመልካም አስተዳደር ቅሬታዎችንም መፍትሔ ለመስጠት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ገልጸዋል። የመንግሥትን ገቢ የመሰብሰብ አቅም በማጎልበት ተጠያቂነትን ከግልጸኝነት ያጣመረ ዘመናዊ የአሰራር ሥርዓት መዘርጋት እንደሚያስችልም ተናግረዋል። የምክር ቤቱ አባላትና የሕግ ማዕከል ባለሙያዎችም፤ በማሻሻያ ረቂቅ አዋጁ የታክስ ስሌት፣ የይርጋ ጊዜ ገደብ፣ የታክስ ከፋይ መስተንግዶና ተያያዥ ጉዳዮችን በማስመልከት ጥያቄ አንስተዋል። በገንዘብ ሚኒስቴር ከፍተኛ የሕግ አማካሪ ዋሲሁን አባተ፤ በረቂቅ አዋጁ የይርጋ ጊዜው አስር ዓመት ሆኖ መቀመጡ በታክስ ከፋዩ ላይ የሚኖረውን ጫና መቀነስ እንደሚያስችል ተናግረዋል። በገንዘብ ሚኒስቴር የሕግ ጉዳዮች መምሪያ ኃላፈ ተወዳጅ መሐመድ፤ የታክስ ደረሰኝ አለመስጠት ተመሳሳይ የገንዘብ ቅጣት መጣሉ ሆን ተብሎ የሚፈጸምን የታክስ ማጭበርበር በማስቀረትና ደረሰኝ መቁረጥን ባህል ያደርጋል ብለዋል። በገቢዎች ሚኒስቴር የታክስ አማካሪ ያሬድ ፍቃደ በበኩላቸው፤ የገለልተኛ አስማሚ ስርዓት ገለልተኛ ሆኖ የሚቋቋም በመሆኑ ግብር ከፋዩ የሚገጥመውን ችግር መፍቻ ተጨማሪ አማራጭ ነው ብለዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጀ፤ የማሻሻያ ረቂቅ አዋጁ ኢኮኖሚው በሚያመነጨው ልክ ገቢን ለመሰብሰብና የታክስ አስተዳደርን ለማዘመን እንደሚያስችል ተናግረዋል። በአስረጂ መድረኩ ግልፅ ያልሆኑ ጉዳዮች ይበልጥ ማጥራት የሚያስችል ማብራሪያ መሰጠቱን ጠቁመው የተደረጉት ማሻሻያዎች ፍትሐዊነትንና የሕግ ተገዢነትን የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል።
የኃይል አቅርቦትን አስተማማኝነትና ዘላቂነት ለማረጋገጥ የፀሃይ ሃይል ልማትን ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 10, 2026 796
አዳማ፤ ሰኔ 3/2018 (ኢዜአ)፡-የኃይል አቅርቦትን አስተማማኝነትና ዘላቂነት ለማረጋገጥ የፀሃይ ሃይል ልማትን ለማስፋፋት ትኩረት መሰጠቱን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ገለፀ። ሚኒስቴሩ አማራጭ የኃይል ምንጮችን ለማስፋፋትና በዘርፉ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎን ለማጠናከር ያለመ የውይይት መድረክ በአዳማ በማካሄድ ላይ ይገኛል ። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) እንደገለፁት ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በታዳሽ ሃይል ልማት ላይ በትኩረት እየሰራች ትገኛለች። በተለይ በውሃ፣ በፀሃይ፣ በንፋስና በጂኦተርማል ሃይል ልማት ላይ ትኩረት መደረጉን ገልጸው በአሁኑ ወቅት 96 በመቶ የሚሆነው የሃይል አቅርቦት ከኃይድሮ ኤሌክትሪክ የሚገኝ መሆኑን ገልጸዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ አስተማማኝና ዘላቂ የሃይል አቅርቦትን ለማረጋገጥ አማራጭ የሃይል ልማት የማስፋፋት ስራ በትኩረት እየተከናወነ ነው ብለዋል። ከአማራጭ ታዳሽ ሃይል ልማት የፀሃይ ሃይል ልማት አንዱ መሆኑን ጠቅሰው ልማቱ ላይ የግሉን ዘርፍና ባለድርሻ አካላትን ለማሳተፍ የሚያስችሉ የህግ ማዕቀፎችና አሰራሮች መዘርጋታቸውን ገልጸዋል። በተለይም የፀሀይ ኃይል ልማቱ አርሶና አርብቶ አደሮች በመስኖና በተለያዩ የስራ መስኮች በዘላቂነት እንዲሳተፉና ህይወታቸው እንዲለወጥ በማድረግ ረገድ ቁልፍና አጋዥ መሆኑንም ተናግረዋል። ከዋና የሃይል መስመር ርቀው የሚገኙ ወረዳዎችና የገጠር ቀበሌዎችን የመብራት ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ ንፁህ የመጠጥ ውሃ እንዲያገኙ ብሎም በመስኖ ልማት እንዲሳተፉ ጭምር ውጤት እየተገኘበት ነው ብለዋል። በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የዩ.ኤን.ዲ.ፒ አፍሪካ ሚኒግሪድ ፕሮግራም ማኔጀር አቶ ይመስላል ተፈራ በበኩላቸው የግሉ ዘርፍ በፀሃይ ሃይል ልማት እንዲሳተፍና ዘርፉ በትብብር እንዲለማ ምቹ ሁኔታን መፍጠር ያስፈልጋል ብለዋል። በተለይ ከህግ ማዕቀፎች ጀምሮ በርካታ የአሰራር ማሻሻያዎች መዘጋጀታቸውን ጠቅሰው የሃይል ዘርፉ አንዱ የኢንቨስትመንት መስክ መሆኑንም ገልጸዋል። በተለይ በግብርና ዘርፍ ብቻ የተወሰኑ የህብረት ስራ ማህበራትና ዩኒየኖች በጸሃይ ኃይል ልማት በመሳተፍ ገበያ ተኮርና የገቢ አቅማቸውን የሚያሳድግ ሰፋፊ የግብርና መስኖ ልማት እንዲያከናውኑ ዕድልን የሚሰጥ መሆኑንም ተናግረዋል። በዚህም ፕሮግራሙ ለህብረት ስራ ማህበራትና ዩኒየኖች በጸሃይ ኃይል ልማት ላይ የአቅም ግንባታ ስልጠና ከመስጠት ባለፈ በፓይለት ደረጃ በሐዋሳ፣ ሶማሌና ቄለም ወለጋ ዞኖች እየሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በኦሮሚያ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ የኢነርጂ አቅርቦት ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ሶሬሳ ከውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ጋር በታዳሽ ሃይል ልማት ማስፋፋት ላይ በትኩረት እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። በተለይ በቄለም ወለጋ ላሎ ቂሌ ወረዳ የሚኒግሪድ የፀሃይ ሃይል ልማት ለማከናወን በትብብር እየተሰራ መሆኑን ገልጸው በተጨማሪም የክልሉ የህብረት ስራ ማህበራትና ዩኒየኖች በፀሃይ ኃይል ልማት እንዲሳተፉ የአቅም ግንባታ ስልጠና እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።
የበጋ መስኖ ልማት በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ የአርስ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳደገ ነው
Jun 10, 2026 429
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የበጋ መስኖ ልማት በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ የአርስ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳደገ መሆኑን የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ ገለጹ። በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ቂምቢቢት ወረዳ በ21 ሺህ 463 ሄክታር መሬት ላይ የለማ የመስኖ ስንዴ ሰብል ስብሰባ ተጀምሯል። በዚሁ ጊዜ ምከትል ፕሬዚዳንቱ እንዳሉት የበጋ መስኖ ሰብል ልማት በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እያገዘ ይገኛል። በኦሮሚያ ክልል እየተከናወነ የሚገኘው የበጋ መስኖ ልማት ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር እንዲሁም የአርሶ አደሩን ገቢ በዕጥፍ እያሳደገ መሆኑን ተናግረዋል። የልማት ስራው ግብርናውን ለማሸጋገር ጭምር እያገዘ መሆኑን ጠቅሰው የግብርና ሜካናይዜሽን ግብዓቶችን በብዛት፣ በጥራት እንዲሁም ፈጠራን መጠቀም እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ዓመታት በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ኢኒሼቲቭ መልክ እየተካሄደ ሲሆን ይህም በክረምት ዝናብ ብቻ ተወስኖ የነበረው የግብርና ባህል መለወጥ እያስቻለ ነው ብለዋል። በዚህ ወቅት የክልሉ አርሶ አደር በሁሉም የልማት ወቅቶች የግብርና ስራን እያከናወነ ሲሆን የገጠር ልማትን ከመሠረቱ ለመቀየር የተጀመረው ስራ ይጠናከራል ነው ያሉት። አቶ አወሉ አብዲ አክለውም በዞኑ በትራክተር ማረስና በኮምባይነር ሰብል የመሰብሰብ ባህል እየተለመደ መጥቷል ብለዋል።
በጋምቤላ ክልል በዘንድሮው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው ውስጥ 72 ከመቶ የሚሆነው መሬት በዘር ተሸፍኗል
Jun 10, 2026 213
ጋምቤላ፤ ሰኔ 3/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በዘንድሮው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው ውስጥ ከ72 በመቶ በላይ የሚሆነው መሬት በዘር መሸፈኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ እስታወቀ። የጋምቤላ ክልል ሰፊ ለም መሬት፣ ከፍተኛ የውሃ አማራጭ እና ለተለያዩ ሰብሎች ተስማሚ የሆነ የአየር ንብረት ያለው በመሆኑ ለግብርና ኢንቨስትመንትም ሆነ በአነስተኛ እርሻ ላይ ለተሰማሩ አርሶ አደሮች ትልቅ አቅም ያለው ነው። በመሆኑም ክልሉ ያለውን ፀጋ በመጠቀም የክልሉን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥና ክልሉ በሀገር ኢኮኖሚ ላይ መጫወት የሚገባውን ሚና እንዲወጣ በርካታ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆኑ ተገልጿል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አንድሮው ቱት ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ በተያዘው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው መሬት አንድም ማሳ ጦም እንዳያድር በሁሉም ዞኖችና ወረዳዎች የተጠናከረ የንቅናቄ ስራ እየተከናወነ ነው። በእስካሁኑ ሂደትም በምርት ዘመኑ ለማልማት ከታቀደው 180 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ 130 ሺህ ሄክታሩ በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች መሸፈኑን ጠቁመው ይህም የእቅዱን 72 ከመቶ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ሁሉም ዞኖችና ወረዳዎች ቀድመው ለሚዘሩ የበቀሎ፣ የሰሊጥ፣ የለውዝና ሌሎች የሰብልና የጓሮ አትክልት የተዘጋጁ ማሳዎች በዘር መሸፈናቸውን ገልጸዋል። በተለይም የበልግ ዝናብን የሚጋሩት በማጃንግ ዞን የሚገኙ የጎደሬና የመንጌሽ ወረዳዎች ያለውን ምቹ ስነ-ምህዳር በመጠቀም ኩታ ገጠምን ጨምሮ የመኸር ግብርና ልማት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። ቀሪውን ማሳ ዘግይተው በሚዘሩ ሰብሎች ለማሸፈንም የባለሙያዎች ስምሪት በማካሄድ የግብዓት አቅርቦትን ጨምሮ የተጠናከረ የድጋፍና ክትትል ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አክለዋል። በምርት ዘመኑ እየለማ ያለው መሬት ከቀዳሚው ዓመት በስምንት ሺህ ሄክታር ብልጫ ያለው መሆኑን ጠቁመው፤ ከዚህም ከ5 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ግብ መጣሉን አቶ አንድሮው ገልጸዋል። በጎደሬ ወረዳ ጎሽኔ ቀበሌ በኩታ ገጠም ልማት የተሰማሩት አርሶ አደር አብረሃም አባተ ከመጋቢት ወር አጋማሽ ጀምሮ የበቆሎ ሰብል በኩታ ገጠም ማልማታቸውንና ሰብሉም በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የግብርና ልማት በኩታ ገጠም ሲሰራ የግብርና ግብዓቶችን ለማግኘትና በሰብል ላይ ጉዳት የሚያደርሱ እንስሳትን ለመከላከል ጭምር የጎላ ጠቀሚታ እንዳለው የገለጹት ደግሞ የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ኢቲባ ድንገታ ናቸው። በዘንድሮው የመኸር እርሻ በኩታ ገጠም ማልማት በመጀመራቸው ምርጥ ዘርና ሌሎች ግብዓቶችን በወቅቱ ማግኘት እንዳስቻላቸውም ተናግረዋል በክልሉ ማጃንግ ዞን በሚገኙ የጎደሬና መንጌሽ ወረዳዎች በኩታ ገጠም የለማ የበቆሎ ሰብል በዘርፉ አመራሮችና ባለሙያዎች ተጎብኝቷል።
በኦሮሚያ ክልል ለመኸር እርሻው እስካሁን ከ4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ተሰራጭቷል
Jun 10, 2026 155
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ለመኸር እርሻው እስካሁን ከ4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ እንዳሻው ጀማነህ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በመኸር እርሻ 11 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር መሬትን በማልማት ከ380 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዷል። አጠቃላይ በመኸር እርሻ ከሚለማው መሬት ውስጥም 8 ነጥብ 9 ሚሊዮን ሄክታሩ በኩታ ገጠም የእርሻ ስነ-ዘዴ የሚለማ መሆኑን ጠቁመዋል። በክልሉ እስካሁን ባለው ሂደት ከ8 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት መታረሱን ጠቅሰው፣ ከዚህ ውስጥ ከ2 ሚሊዮን 823 ሺህ በላይ ሄክታሩ በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች መሸፈኑን ተናግረዋል። በምርት ዘመኑ የታቀደውን ግብ ለማሳካት የግብዓት አቅርቦቱ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። ለመኸር እርሻው ከ14 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ለማቅረብ ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን ጠቅሰው፣ እስካሁን ከ8 ሚሊዮን 454 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ በሕብረት ሥራ ማህበራትና በዩኒየኖች በኩል እየተሰራጨ መሆኑን ተናግረዋል። ለማህበራቱና ለዩኒየኖቹ ከደረሰው ማዳበሪያም ከ4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሚሆነው ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ገልጸዋል። ከታቀደው 2 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ውስጥ 378 ሺህ 426 ኩንታሉ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች የደረሰ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 355 ሺህ 73 ኩንታሉ ለአርሶ አደሩ በወቅቱ ተከፋፍሏል ብለዋል። በክልሉ በአሁኑ ወቅት ያለው የዝናብ ሁኔታ መልካም በመሆኑ፣ አርሶ አደሩ ይህንን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በእርሻ ሥራው ላይ በንቃት እየተሳተፈ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። ለመኸር እርሻው ስኬታማነት ከክልል እስከ ታችኛው መዋቅር የሚገኙ አመራሮችና የግብርና ባለሙያዎች ለአርሶ አደሩ የቅርብ ክትትልና ጠንካራ ሙያዊ ድጋፍ እያደረጉ መሆኑንም አቶ እንዳሻው ጨምረው ገልጸዋል።
በቆሻሻ አወጋገድና መልሶ አጠቃቀም ላይ የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች የአዲስ አበባን የጽዳትና የአረንጓዴ ልማት ደረጃ እያሳደጉ ነው
Jun 10, 2026 142
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2018(ኢዜአ)፦ በቆሻሻ አወጋገድ እና መልሶ ጥቅም ማዋል ላይ የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች የአዲስ አበባን የጽዳት እና የአረንጓዴ ልማት ደረጃ እያሳደጉ መሆኑን የአዲስ አበባ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። በተጨማሪም ለከተማዋ ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር በኩልም ጉልህ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ ተመላክቷል። 'ሪች ፎር ቼንጅ ኢትዮጵያ' የተሰኘ ዓለምአቀፍ ድርጅት ከአይኬኢኤ ፋውንዴሽን ጋር በመተባበር “የኢትዮጵያ አረንጓዴ መጻኢ ዕድል፦ በኢትዮጵያ የቆሻሻ አወጋገድ እና ሰርኩላር ኢንተርፕራይዞችን መገንባት” በሚል መሪ ሀሳብ ቆሻሻን ወደ ቢዝነስ ለመቀየር ያሰለጠናቸውን ሥራ ፈጣሪዎችን ያስመረቀ ሲሆን አዲስ ሰልጣኞችም አቀባበል ተደረጎላቸዋል። በምረቃ መርሃ-ግብሩ የተገኙት የአዲስ አበባ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ስራ አስፈጻሚ እሸቱ ለማ(ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ በከተማዋ ቆሻሻን ወደ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እንዲቀይሩ በማድረግ በኩል አበረታች ሥራ እየተሰራ ነው። ይህም እንደ ሀገር በፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ውስጥ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የሚደረገውን ጥረት በተግባር የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል። በቆሻሻ አወጋገድ እና መልሶ ጥቅም ማዋል ላይ የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞች የአዲስ አበባን የጽዳት እና የአረንጓዴ ልማት ደረጃ ከማሳደግ ባሻገር ለወጣቶች ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር በኩል ጉልህ ሚና እየተጫወቱ መሆኑን ተናግረዋል። ባለስልጣን መሥሪያ ቤቱም መሰል ስራ ፈጣሪዎችን እና የፈጠራ ሃሳቦችን በፖሊሲ፣ በማበረታቻ እንዲሁም ከባለድርሻ አካላት ጋር በማስተሳሰር የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የ'ሪች ፎር ቼንጅ ኢትዮጵያ' ካንትሪ ዳይሬክተር መቅድም ጉልላት በበኩላቸው፤ ወደ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለሚደረገው ሽግግር ቀጣይነት ያለው የፈጠራ ሥራ፣ ትብብር እና ኢንቨስትመንት የሚጠይቅ መሆኑን አስገንዝበዋል። ሥራ ፈጣሪዎች የአካባቢ ጥበቃ ተግዳሮቶችን የሚፈቱ ተግባራዊ መፍትሄዎችን በማዘጋጀትና ለማህበረሰቡ ሰፊ የኢኮኖሚ ዕድሎችን በመፍጠር በኩል ወሳኝ ሚና እንዳላቸው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ቀጣናዊ ደህንነትን በማረጋገጥ በትብብር ላይ የተመሰረተ የጋራ ዕድገትን ይፈጥራል
Jun 10, 2026 264
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ቀጣናዊ ሰላምና ደህንነትን በማረጋገጥ በትብብር ላይ የተመሰረተ የጋራ ዕድገትን እንደሚፈጥር የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል እና ምሁር ገለጹ። ኢትዮጵያ ከሦስት አስርት ዓመታት በፊት ከዓለም ጋር የምትገናኝባቸው የብዝሃ ባሕር በርና የባሕር ዳርቻ መዳረሻ ወደብ ባለቤት እንደነበረች በታሪክ ተሰንዶ ይገኛል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሠላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ላይ የተፈጸመው በደል የሚያስቆጭ ነው። በኢትዮጵያ ሀገራዊ ለውጥ ማግስት የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ መነሳቱም ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት፣ የህዝብ ቁጥርና የደኅነነት ስጋቶችን መቀልበስ የሚስችል ትብብር ከማጎልበት የሚመነጭ መሆኑን ገልጸዋል። ሀገራዊ ለውጡም ለበርካታ ዓመታት በህዝብ ልብ ተዳፍኖ የቆየውን ታሪካዊ፣ ፍትሐዊ፣ ሕጋዊና መልክዓ ምድራዊ የባህር በር ባለቤትነት ግልጸኝነት መፍጠሩን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ሰላማዊ፣ ሕጋዊና የጋራ ተጠቃሚነት መርህን ተከትሎ መቅረቡም ዓለምአቀፍ ቅቡልነትና ምክንያታዊነት ማጉላቱን አስረድተዋል። በቀጣይም ቀጣናዊ ደህንነት፣ ዓለምአቀፍ ስምምነቶችን፣ በጥናትና ምርምር ላይ የተመሰረተ የዲፕሎማሲ ድርድር አቅምን በማጎልበት ለጥያቄው ምላሽ ማስገኘት እንደሚገባ መክረዋል። ዜጎችም የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት በተለያዩ አማራጮች ለዓለምአቀፍ ማህበረሰብ በማስገንዘብ ብሔራዊ ጥቅምን ማስጠበቅ እንደሚያስፈልግ አንስተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ቀጣናዊ ሰላምና ደህንነትን በማረጋገጥ የጋራ ዕድገትና ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ ትብብር እንደሚፈጥር ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ መከላከያ ኮሌጅ ተመራማሪና መምህር ፕሮፌሰር አየለ በከሪ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ጥንታዊ ስልጣኔና ሃያልነት ከነበራት የባህር በር ባለቤትነት ጋር በጥብቅ የተቆራኘ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ታሪካዊ፣ ሕጋዊ፣ መልክዓ ምድራዊና ተፈጥሯዊ የባሕር በር ባለቤትነትም ከቀይ ባሕር፣ ገልፍ ኦፍ ኤደን እና ሕንድ ውቅያኖስ ጋር ጭምር የተሰናሰለ እንደነበር አስታውሰዋል። ከሶስት አስርት ዓመታት በፊት ተዳፍኖ የነበረው የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ መነሳቱም ኢትዮጵያን ከስልጣኔና ሃያልነቷ የማስታረቅ ብሔራዊ አጀንዳ መሆኑን ገልጸዋል።
የወልድያ ሕዝብና አመራር ለፈተና ሳይበገሩ ከተማዋን ወደ ዘመናዊ የልማት ማዕከልነት እየቀየሩ ነው - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Jun 9, 2026 827
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 2/2018(ኢዜአ)፦ የወልድያ ከተማ ሕዝብና አመራር ሰው ሠራሽ ፈተናዎችን በጽናት በመቋቋም ከተማዋን ወደ ዘመናዊ የልማት ማዕከልነት መቀየር መቻላቸውን የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ይህንን የገለጹት በወልድያ ከተማ የተገነቡ ልዩ ልዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት በበቁበት መርሃ ግብር ላይ ባደረጉት ንግግር ነው። ርዕሰ መስተዳድሩ ከተማዋ የጀግኖች ታሪክ የሚዘከርባት፣ ሕብረ-ብሔራዊ ወንድምና እህት ሕዝቦች በፍቅርና በአንድነት የሚኖሩባት የኢትዮጵያዊነት መገለጫ መሆኗን ገልጸዋል። ከተማዋ በተደጋጋሚ ያጋጠሟትን ፈተናዎች ተቋቁማ፣ በአንድ እጇ ሰላምን በሌላ እጇ ልማትን ይዛ መጓዟን አብራርተዋል። ዛሬ የተመረቁ የልማት ፕሮጀክቶች የወልድያ ከተማን ገጽታ የቀየሩ መሆናቸውን ነው ርዕሰ መስተዳድሩ የጠቀሱት። ታዳጊዎች ስለ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እና ስለ ወደፊት ቴክኖሎጂ ያላቸው የእውቀት መሻት ከተማዋ ለነዋሪዎቿ ምቹ ከመሆን ባለፈ ራዕይ ያላቸው ዜጎችን ለመቅረጽ እየሠራች መሆኑን ማሳያ ነው ብለዋል። ይህ በፈተና ውስጥ ሆኖ የመሥራት ልምድ ሌሎች የክልሉ ከተሞችና ወረዳዎች ሊማሩበትና የሥራ መነሻ ሊያደርጉት የሚገባ መሆኑን በአጽንኦት ጠቅሰዋል። ወልድያ ገና ብዙ ልማት እንደሚገባትና በአራቱም አቅጣጫዎች ለንግድ ምቹ የሆነ ስትራቴጂካዊ አቀማመጧን ታሳቢ ያደረገ ጉዞን ማፋጠን እንደሚገባም አንስተዋል። በሼህ መሐመድ ሁሴን አሊ አል-አሙዲ የተገነባው ዘመናዊ ስታዲየም ከፍተኛ እድሳት እንደሚፈልግና ከተማዋን የስፖርትና ቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ ለስታዲየሙ የሚመጥኑ ዘመናዊ ሆቴሎች ሊገነቡ እንደሚገባ አመላክተዋል። የከተማዋን ዘላቂ ሰላም ማረጋገጥ ከተቻለ ከዚህ የላቀ ልማት ማምጣት እንደሚቻልም ገልጸዋል። የወልድያ ከተማ ከንቲባ ዱባለ አብራሬ በበኩላቸው፤ ከተማዋን ለነዋሪዎቿ ምቹና ፅዱ ማድረግ ያስቻሉ አስደናቂ የልማት ሥራዎች መሰራታቸውን ተናግረዋል። የወልድያ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትም የከተማዋ ነዋሪዎች ፈጣን የመንግሥት አገልግሎት የሚያገኙበትን ምኅዳር የሚፈጥር መሆኑን አስረድተዋል። በልማት ፕሮጀክቶች ምረቃ መርሃ ግብሩ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ እና የአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ ዕዳዎቿን እያራገፈች ተስፋዎቿን እየጨበጠች ወደፊት እየገሰገሰች ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Jun 9, 2026 520
አዲስ አበባ ፤ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ዕዳዎቿን እያራገፈች ተስፋዎቿን እየጨበጠች ወደፊት እየገሰገሰች ነው ሲሉ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወልድያ ከተማ የተገነቡ ልዩ ልዩ የልማት ፕሮጀክቶችን መርቀው ለአገልግሎት ከፍተዋል። በምረቃው ወቅትም እንደገለጹት የተመረቁት የልማት ፕሮጀክቶች የሀገሪቱን ወደፊት የመገስገስ ጉዞ የሚያሳዩና የኢትዮጵያን ዕድገት ማንም ሊያስቆመው እንደማይችል ማረጋገጫዎች ናቸው። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የወልድያ ከተማ ሕዝብ ጽንፈኝነትንና ከፋፋይነትን በመቃወም የሚታወቅ፣ ምርጫው ሰላምና ጠንካራ መንግሥት መሆኑን በየጊዜው ማሳየቱን ገልጸዋል። መንግሥት ትግሉ ከተወሰኑ አካባቢ ሽፍቶች ጋር ሳይሆን መንገዳቸውን ክፍፍልና ድህነት ካደረጉ ቆሞ ቀር ኃይሎች ጋር መሆኑን ጠቅሰዋል። ላለፉት 50 እና 60 ዓመታት ያረጀ አስተሳሰብ ይዘው የቆሙ አካላት የሀገሪቱን ፈጣን ጉዞ መገንዘብ እንዳልቻሉም አስረድተዋል። በጫካ ያሉ አካላት የኮሪደር ልማትን፣ የሌማት ትሩፋትን፣ የገበታ ፕሮጀክቶችንና የስንዴ አብዮትን የመሰሉ በሀገሪቱ የመጡ ታላላቅ ለውጦችን ለማየት እንዳልታደሉ ገልጸዋል። በከተሞች የሚካሄደው የኮሪደር ልማት የውበት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ከተሞችን የማዘመንና የሕዝብን የኑሮ ደረጃ ከፍ የማድረግ ዓላማ በማንገብ በመስፋፋት ላይ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ከተሞች ፉክክር ከምሥራቅ አፍሪካና ከዓለም ከተሞች ጋር መሆን እንዳለበት የገለጹ ሲሆን፤ አገልግሎትን ለማዘመንም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በመላ ሀገሪቱ እየተስፋፋ መሆኑን ጠቁመዋል። በወልድያ ከተማ የተገነቡት የሕዝብ ቤተ መጻሕፍት፣ የዲጂታል ቤተ መጻሕፍትና የሳይንስ ካፌዎች ትውልዱን ከዕለት መረጃ ወደ ጥልቅ ዕውቀትና ምርምር የሚያሸጋግሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። የገበያ ማዕከላትና የሱቆች ፕሮጀክቶች የንግድ እንቅስቃሴን በማሳለጥ ከፍተኛ ሚና እንዳላቸውና በሌማት ትሩፋት አማካኝነትም በምግብ ራስን የመቻል ጉዞው ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አሳስበዋል። ኢትዮጵያ ዕዳዎቿን እያራገፈችና ተስፋዎቿን እየጨበጠች መጓዟን እንደምትቀጥል የገለጹት አቶ ተመስገን፣ ጠላት ቢሰበሰብ የሀገሪቱን ጉዞ ማደናቀፍ እንደማይችል አጽንኦት ሰጥተዋል። የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን ወደ ገጠር ጭምር በማስፋፋት የሀገሪቱን ብልጽግና እውን ለማድረግ መንግሥት፣ ባለሃብቱና ሕዝቡ በጋራ ሊሠሩ እንደሚገባ ጥሪ አቅርበዋል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በወልድያ ከተማ የልማት ፕሮጀክቶችን መረቁ
Jun 9, 2026 321
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፦ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በወልድያ ከተማ የልማት ፕሮጀክቶችን ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፤ የኢትዮጵያ ጉዞ ወደፊት ነው። ጠላት የፈለገውን ያህል ቢያቅድ ከጉዟችን እንደማያስቆመን ወልድያ ምስክር ናት ብለዋል። ዛሬ በታሪካዊቷ፣ በየጁዎች ሥልጣኔ መገኛ በሆነችው ወልድያ ከተማ በመገኘት፣ አመራርና ሕዝብ በአንድነት ተግቶ ያሳካቸውን የልማት ፕሮጀክቶች መመረቃቸውን ገልጸዋል። ወልድያ የልማት፣ የፅናትና የድል አምባ ናት ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተማዋን የማዘመን፣ የኮሪደር ልማትን የማስፋፋት፣ የሕዝብና የዲጂታል ቤተ-መጻሕፍትን የመገንባት እንዲሁም የንግድና የኢንዱስትሪ ማዕከላትን እውን የማድረግ ሥራዎቻችን ወደፊት የመገስገሳችን ማረጋገጫዎች ናቸው ሲሉም ተናግረዋል። መንገዳችን መደመር፣ ግባችን ደግሞ ብልጽግና ነው! ትግላችን መንገዳቸውን ክፍፍል፣ ግባቸውን ድህነት ካደረጉ ቆሞ-ቀሮች ጋር በመሆኑ የኢትዮጵያን ልዕልና ሳናረጋግጥ አንቆምም ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው። ሺህ ጠላት ቢሰበሰብ የኢትዮጵያን ጉዞ ለአፍታም እንደማያስቆመው አስገንዝበዋል።
የዕቃ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓት ደንብ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እያደረገ ነው
Jun 9, 2026 325
አዲስ አበባ፤ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፦የዕቃ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓት ደንብ የግብርና ኢኮኖሚ ሽግግርን በማሳለጥና የገጠር ልማትን በማጎልበት አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ ታዜር ገብረእግዚአብሔር ገለጹ፡፡ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር በዕቃ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓት ደንብ ቁጥር 589/2018 ዓ.ም ዙሪያ የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ እያካሄደ ይገኛል። ይህ ሥርዓት አርሶ አደሮች፣ ማኅበራትና አቀናባሪዎች ደረጃውን የጠበቀ ምርት በመጋዘን አስቀምጠው በደረሰኝ አማካኝነት የባንክ ብድር የሚያገኙበት አሠራር ነው። አሠራሩ አርሶ አደሮች በምርት መሰብሰቢያ ወቅት የሚገጥማቸውን የገንዘብ ዕጥረት ለመቅረፍ በኢትዮጵያ ሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ አማካኝነት ተግባራዊ ሆኗል። ቀደም ሲል አርሶ አደሮች በገንዘብ እጥረት ምርታቸውን በርካሽ ዋጋ ለመሸጥ ይገደዱ የነበረ ሲሆን፣ ይህም በምርታማነትና በሀገር ኢኮኖሚ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሯል። አዲሱ አሠራር ግን አርሶ አደሮች ምርታቸውን በደረሰኝ በማስያዝ ብድር እንዲያገኙና በተሻለ ዋጋ በመሸጥ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እንዲያሳድጉ ያስችላቸዋል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ ታዜር ገብረእግዚአብሔር እንዳሉት፤ ሥርዓቱ የገጠርና የግብርና ልማት ሽግግርን በማፋጠን አስተማማኝ የፋይናንስ አቅርቦት ዕድል የሚፈጥር ነው። ሥርዓቱ ከ20 ዓመታት በላይ ቢያስቆጥርም ግልፅ ተቆጣጣሪ ባለመኖሩ የቆየ ሲሆን፣ አሁን ግን መንግሥት በሕግና መመሪያ ባለቤት በማበጀት ተግባራዊ አድርጎታል ብለዋል። አርሶ አደሮች ምርታቸውን በአስተማማኝ ሁኔታ በማከማቸት ብድር ማግኘት እንዲሁም መቼና እንዴት መሸጥ እንዳለባቸው የማሰቢያ ጊዜ እንደሚሰጣቸው ተናግረዋል። ሥርዓቱንም በቴክኖሎጂ የተደገፈ አሰራር እንዲሆን በማስቻል የፋይናንስ ተቋማትን የሚያበረታታ ደንብ፣ መምሪያና የቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋቱን አስረድተዋል። የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት (አግራ) የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ይኼነው ዘውዴ (ዶ/ር) የደረሰኝ ሥርዓቱ የአርሶ አደሮችን ድካም የሚመጥን የተሻለ ገበያና ዋጋ ማግኘት የሚያስችል ነው ብለዋል። አሠራሩ ምርታማነትን በማሻሻል፣ በተመዘገበ መጋዘን ለሚቀመጥ ምርት በደረሰኙ የብድር ዋስትና የሚያገኙበትን ዕድል በመፍጠር የአርሶ አደሮችን የመደራደር አቅም ያሳድጋል ብለዋል። የብድር መስፈርቶች የአርሶ አደሮችና ማኅበራትን ነባራዊ ሁኔታ ታሳቢ ማድረግ እንዳለባቸው የጠቆሙት ዳይሬክተሩ፣ ሥርዓቱ የአርሶ አደሩን ሕይወት በመቀየር የግብርና ሽግግርን ያሳካል ብለዋል። አግራ ግብርናን ለማዘመን ከአፍሪካ ሕብረት ጋር በ15 ሀገራት እየሠራ መሆኑን ገልጸው፣ ለኢትዮጵያ የዕቃ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓት ውጤታማነትም በትብብር እንደሚሠራ አረጋግጠዋል። የኦሮሚያ ህብረት ሥራ ባንክ ምክትል ፕሬዝዳንት ዮሐንስ አምቢሳ ፤የዕዳ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓት ደንብ ለባንኮች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸዋል፡፡ አርሶ አደሮችና ህብረት ሥራ ማህበረት የብድር ማስያዣ ችግር ይገጥማቸው እንደነበር ገልጸው፤ ባንኮች የደረሰኝ ሥርዓቱን ብቻ በመያዝ ብድር ማቅረብ ይችላሉ ብለዋል፡፡ የአማራ ባንክ የብድር ክፍል ኃላፊ እሸቴ የማታ፤ በበኩላቸው ባንኮች የዕዳ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓቱን እንደ ብድር ምርት ማድረጋቸው በአርሶ አደሮችና ባንኮች መካከል መተማመንን ይፈጥራል ብለዋል፡፡ የዕዳ ማከማቻ ደረሰኝ ሥርዓት ደንብ ለባንኮች አስተማማኝ የማበደር ዋስትና እና ለአርሶ አደሮች ደግሞ እፎይታን እንደሚሰጥ ገልጸዋል፡፡
በክልሉ የማዕድን ሀብት ልማት ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል እየፈጠረና ከፍተኛ የገቢ አቅም እየሆነ ነው
Jun 9, 2026 112
ባህር ዳር፤ ሰኔ 2/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የማዕድን ሀብት ልማት ዘርፉ በጥናትና ምርምር በመታገዙ ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል እየፈጠረና ከፍተኛ የገቢ አቅም እየሆነ መምጣቱን የክልሉ ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ ገለጸ። ቢሮው በክልሉ ከሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር የሥነ ምድር ጥናትና ካርታ ስራ እንዲሁም የማዕድን ፍለጋና ክምችት ግመታ ጥናት የውል ፊርማ ስነ-ስርዓት አካሂዷል። የቢሮ ኃላፊው ሀይሌ አበበ በመድረኩ እንደገለፁት፤ በክልሉ የማዕድን ሀብት ልማቱን በጥናትና ምርምር በማስደገፍ በተሰራ ስራ ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል እየፈጠረና ከፍተኛ የገቢ አቅም እየሆነ ነው። በዚህም በክልሉ የግራናይት፣ የማርብል፣ የጅብሰም፣ የወርቅ፣ የብረትና ሌሎች ማዕድናት በጥናት መለየታቸውን አብራርተዋል። ዘርፉን በጥናትና ምርምር በመለየትና በማልማት ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሬን ለማሳደግ መዋላቸውንም ገልፀዋል።ዘርፉ ለስራ ዕድል ፈጠራና ኢንቨስትመንቱ እንዲነቃቃ በማድረግ በኩል ተጨባጭ ለውጥ መመዝገቡን አመልክተዋል። በቀጣይም የዘርፉን የመልማት አቅም በጥናትና ምርምር ውጤቶች ላይ በመመርኮዝ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ በቅንጅት ይሰራል ነው ያሉት። የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዚዳንት ተወካይ ውለታው መኩሪያ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንደገለጹት፤ ዩኒቨርሲቲው የማዕድን ልማትን በምርምር እያገዘ ይገኛል። በምርምር ላይ መሰረት ያደረገ የሃብት ፍለጋ ስራ በትብብር መከናወኑ ዘላቂ ዕድገትን ለማስመዝገብ ያስችላል ብለዋል። የማዕድን ሃብት ልማት ስራው ምርምርና እውቀትን መሰረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑ የሚበረታታ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የወሎ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት ሃዋ ወሌ (ዶ/ር) ናቸው። በክልሉ ያሉትን የማዕድን ሀብቶች በእውቀት ለይቶ ለማልማት በሚደረገው ጥረት ዩኒቨርሲቲው በትብብር እየሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። የውል ስምምነቱ የተካሄደው ከባህር ዳር፣ ጎንደር፣ ወልዲያ፣ ወሎ፣ ደብረ ብርሃን እና ደብረ ማርቆስ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር ነው።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በወልድያ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን ይመለከታሉ
Jun 9, 2026 273
አዲስ አበባ፤ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፦ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን ለመመልከት ወልዲያ ከተማ መግባታቸውን ገልጸዋል። ምከትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ የታላቁ ራስ ዓሊ ከተማ፣ የየጁዎች ሥልጣኔ መገኛ፣ የአራቱ አውራ መንገዶች መገናኛ፣ ተራሮች እንደ ሐረግ ከተጋመዱባት፣ የሰሜን ምሥራቅ ኢትዮጵያ ንግድ ማዕከል በሆነችው የጥንቷ ገነቴ፣ የአሁኗ ወልድያ ከተማ ገብተናል ብለዋል። ጎበዝና ቆንጆ ከሚወለዱባት፣ታሪክና ትውፊት ከተከማቸባት፣ ከመስጠት በስተቀር ስስት ከሌለባት ወልድያ ስንደርስ በአካባቢው ወግ መሰረት ደማቅ አቀባበል ላደረጉልን ለክልሉ ርዕሰ መስተዳድር፣ ለካቢኔያቸው፣ ለወልድያ ከተማ ከንቲባ እና ለከተማዋ ነዋሪዎች ከልብ የመነጨ ምስጋና ለማቅረብ እወዳለሁ ያሉ ሲሆን በወልድያ በሚኖረን ቆይታ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን የምንጎበኝ ይሆናል ነው ያሉት።
በክልሉ የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር ለማር ምርት እድገት አስተዋጾ አድርጓል
Jun 9, 2026 148
ባህር ዳር፤ ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር ለማር ምርት እድገት አስተዋጾ ማድረጉ ተገለጸ። በክልሉ ባለፉት አስር ወራት 33 ሺህ ቶን ማር መመረቱ ተመላክቷል። የክልሉ እንስሳትና ዓሳ ሃብት ልማት ቢሮ የንብና ሀር ልማት ባለሙያ አቶ ሙሀመድ ጌታሁን ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በክልሉ እየተተገበረ የሚገኘው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለማር ምርት እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል። በመርሃ ግብሩ ትኩረት ሰጥቶ ከሚሰራባቸው ዘርፎች አንዱ የንብ ማነብ መሆኑን ጠቁመው በዘርፉ ከ500 ሺህ በላይ አባወራዎች፣ የተደራጁ ወጣቶችና ሴቶች እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል ። በበጀት አመቱ አስር ወራት የንብ መንጋ ከያዙ 1 ነጥብ 9 ሚሊዮን ዘመናዊ፣ የሽግግርና ባህላዊ ቀፎዎች 33 ሺህ ቶን ማር መገኘቱን አስታውቀዋል። የተገኘው የማር ምርት በበጀት አመቱ ለማምረት ከታቀው በላይ መሆኑን ጠቁመዋል ። የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር ትግበራ ለንብ ማነብ የፈጠረው ምቹ ሁኔታ ለማር ምርት እድገት አስተዋጾ ማድረጉን አመልክተዋል። በዘርፉ የገበያ ትስስር በመፍጠር የአናቢዎችን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው ብለዋል። በዋግ ኽምኸራ ብሔረሰብ አስተዳደር በደሀና ወረዳ ቀበሌ 01 ነዋሪ አርሶ አደር አለባቸው በላይ እንዳሉት፣ በ21 ዘመናዊና በ26 ባህላዊ ቀፎዎች በመታገዝ በንብ ማነብ ስራ ተሰማርተዋል። ዘንድሮ 410 ኪሎ ግራም ማር አምርተው በመሸጥ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። በምስራቅ ጎጃም ዞን በሸበል በረንታ ወረዳ የመዝን ኪሮስ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ላቃቸው ደግዋለ በበኩላቸው በ42 ዘመናዊና ባህላዊ ቀፎዎች የንብ ማነብ ስራ እያከናወኑ መሆኑን አመልክተዋል። ዘንድሮ እስካሁን ያመረቱን ከ170 ኪሎ ግራም በላይ ማር ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ገቢ ማግኘታቸውን ገልጸዋል።
በሶስተኛው ዙር የጀመርናቸውን 13.4 ኪሜ የሚሸፍነውን የኮሪደር ልማት ስራዎችን አፈፃፀም ገምግመናል-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jun 9, 2026 228
አዲስ አበባ፤ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፦ከንቲባ አዳነች አቤቤ ዛሬ ማለዳ በሶስተኛው ዙር የተጀመረውን 13.4 ኪሜ የሚሸፍን የኮሪደር ልማት ስራ አፈፃፀም መገምገማቸውን ገለጹ። የኮሪደሮቹ ልማት በአምስት መስመሮች ተከፋፍለዉ እየተሰሩ ሲሆን እነርሱም፦ 1- ከቦሌ መድሃኔዓለም እስከ ጎላጎል ( የቦሌ አትላስን መንገድ ከመስቀል አደባባ መገናኛ መንገድ ጋር የሚገናኝ)፣ 2- ከጎላጎል እስከ እንግሊዝ ኤምባሲ (የቀበና መገናኛ መንገድን ከመስቀል አደባባ መገናኛ መንገድ ጋር የሚገናኝ) ፣ 3- ከቦሌ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት በሞኤኮ እስከ ቦሌ መገናኛ መንገድ ( የቦሌ አትላስን መንገድ ከቦሌ መገናኛ መንገድ ጋር የሚገናኝ)፣ 4- ከኢምፔሪያል በአደይአበባ ስቴድዮም እስከ ሻላ መናፈሻ ፣ 5-ከውሃ ልማት በአትላስ ያለውን እና ከአትላስ እስከ ቦሌ ሩዋንዳ ( የቦሌ አትላስ መንገድን ከመስቀል አደባባ መገናኛ መንገድ እና ከቦሌ አየርመንገድ ጋር የሚገናኝ) በከፍተኛ ደረጃ የመንገድ ትስስርን የሚያሰፋ፣ የንግድ ተቋማት ፣ ሰፋፊ የእግረኛ መንገድ፣ የሳይክል መንገድ እና ለትራንስፖርት አገልግሎት ምቹ እንዲሆኑ ተደርገው እየተገነቡም ናቸው። በተጨማሪም በርካታ የህዝብ አገልግሎት መስጫ ግንባታዎችን የያዘ ሲሆን የግንባታውም ሂደትም በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛል። በአደይአበባ ስታዲየም ዙሪያ አስቀድመው የተጀመሩ የኮሪደርና ሌሎች መሠረተ ልማት ግንባታዎች በፍጥነትና በጥራት እንዲከናወኑ የማድረግ ስራ ተጠናክሮ ቀጥሏል። ከኮሪደሩ በተጨማሪም ለብዙ ዘመናት ተረስቶ የኖረ፣ ከሕዝብ ተወስዶ በግለሰቦች ያለአግባብ ተወሮ ለብዙ ብልሽት ተዳርጎ የኖረውን ቦታ ለህዝብ አገልግሎት እንዲውል ተደርጎ በመሰራት ላይ ይገኛል። ፕሮጀክቶቹን እስከ ሰኔ ወር መጨረሻ ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ለአገልግሎት ለማዋል በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል።
ቴክኖሎጂን ከሀገራዊ ርዕያችን ጋር ማጣመራችን ለሀገር የሚገባውን ፈጣን እድገት እውን ለማድረግ በትክክለኛው አቅጣጫ ላይ መሆናችንን ያሳያል-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jun 9, 2026 199
አዲስ አበባ፤ሰኔ 2 /2018 (ኢዜአ)፦ቴክኖሎጂን ከሀገራዊ ርዕያችን ጋር ማጣመራችን ለሀገር የሚገባውን ፈጣን እድገት እውን ለማድረግ በትክክለኛው አቅጣጫ ላይ መሆናችንን ያሳያል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። በሚኒስትሮች ምክር ቤት ስብሰባ ማጠቃለያ ላይ እጅግ ዘመናዊና ፈጣን የቴክኖሎጂ ግብዓቶችን በመጠቀም የተገነቡ ቤቶች የሚገኙበት የግንባታ ሳይት ጉብኝት ማድረጋቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው ላይ አስፍረዋል። በዚህ ሳይት ሦስት የላቁ የግንባታ ዘዴዎች በጥምረት ጥቅም ላይ የዋሉ ሲሆን፣ እነሱም የ3ዲ ህትመት (3D printing)፣ የቅድመ-ዝግጅት ቀላል የአረብ ብረት ግንባታ እና የኮንቴይነር መኖሪያ ቤቶች መሆናቸውን ገልጸዋል። እያንዳንዳቸው ግንባታዎች ትክክለኛውን ቴክኖሎጂ ስንጠቀም ፍጥነት እና ጥራት እርስ በእርስ የማይጋጩ መሆናቸውን ያረጋገጡ መሆናቸውን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፤ ጥራታቸውን የጠበቁ መኖሪያ ቤቶችን ከወራትና ከዓመታት ይልቅ በጥቂት ቀናት እና ሳምንታት ውስጥ ሰርቶ ማጠናቀቅ እንደሚቻል የታየበት ህያው ምስክር መሆኑንም አስታውቀዋል። ይህ አይነቱ የላቀ ፈጠራ በየትኛውም የሀገሪቱ ክፍል በቀላሉ ሊተገበር፣ ሊደገም እና ሊስፋፋ የሚችል መሆኑንም ያብራሩት። ይህም የሀገራችንን የቤት ልማት ፕሮግራም አቅጣጫ በከፍተኛ ደረጃ የመቀየር ኃይል አለው ብለዋል። ቴክኖሎጂን ከሀገራዊ ርዕያችን ጋር ማጣመራቸውን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፤ መሰል በተግባር የተገለጡ ስራዎቻችን ደግሞ ለሀገር የሚገባውን ፈጣን እድገት እውን ለማድረግ በትክክለኛው አቅጣጫ ላይ በቁርጠኝነት እየተጓዝን መሆናችንን በተግባር ያሳዩ መሆናቸውን አስገንዝበዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት መረጋገጥ ኢኮኖሚያዊ ሉዐላዊነቷን እንድታስከብር መሰረት ይጥላል
Jun 9, 2026 104
ሆሳዕና፤ ሰኔ 2/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት መረጋገጥ የኢኮኖሚ ሉዐላዊነቷን ለማስከበር መሰረት ይጥላል ሲሉ የዋቸሞ እና የወራቤ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለፁ። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ የዜጎችን ንቁ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑንም ምሁራኑ ተናግረዋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ የዋቸሞ እና የወራቤ ዩኒቨርሲቲ ምሁራንን ሞያዊ ማብራሪያ ጠይቋል። በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር ዳንኤል ሀንዲኖ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት ኢትዮጵያ ከባህር በር ተነጥላ እንድትኖር የተደረገበት ኢፍትሃዊ መንገድ ቅቡልነት የለውም። በዚህም ላለፉት ዓመታት ለተለያዩ ችግሮች ተዳርጋ ቆይታለች ያሉት ዳንኤል (ዶ/ር)፣ ከዚህ ችግር ለመውጣት መንግስት በዲፕሎማሲያዊ መንገድና በሰጥቶ መቀበል መርህ የጀመረው ጥረት እንዲሳካ የሁሉም አስተዋጾ መጠናከር አለበት ብለዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት መረጋገጥ የኢኮኖሚ ሉዐላዊነቷን ለማስከበር መሰረት እንደሚጥል ገልጸው፣ ጥያቄው ታሪካዊ እና ህጋዊ መሰረት ያለው ከመሆኑ ባለፈ ለሀገር እድገት ፋይዳው የጎላ በመሆኑ አፋጣኝ ምላሽ ይፈልጋል ብለዋል። መንግስት ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ የባህር በር ባለቤት ለመሆን ያላትን ጽኑ ፍላጎት ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ያስገነዘበበት ሂደት የሚደገፍና የሚበረታታ መሆኑንም ነው የገለጹት፡፡ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ባለፈ የህልውና ጉዳይ በመሆኑ ዜጎች አስተዋጿቸውን ማጠናከር አለባቸው ብለዋል። ሌላው በወራቤ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር አባስ ሉቅማኔ በበኩላቸው እንዳሉት፣ እንደ ኢትዮጵያ ላሉ በፈጣን እድገት ላይ ለሚገኙ ሀገራት የባህር በር ጉዳይ ለድርድር የሚቀርብ አይደለም። በአሁኑ ወቅት ከ130 ሚሊዮን በላይ የህዝብ ቁጥር ያላትን ኢትዮጵያ የባህር በር ማሳጣት እድገቷ በተፈለገው ፍጥነት እንዳይሄድ ይገድባል ሲሉም ጠቁመዋል። ለዘመናት የባህር በር ባለቤት የነበረች ሀገር ላለፉት በርካታ ዓመታት ከባህር በር እንድትነጠል መደረጉ ከፍተኛ ገንዘብ ለወደብ ኪራይ እንድታወጣ ከማድረጉ ባለፈ በወጭና ገቢ ንግድ እንቅስቃሴ ላይም ተጽዕኖ አሳድሯል ብለዋል። ኢትዮጵያ ከዚህ ችግር ለመውጣት ዓለም አቀፍ ህግንና ታሪካዊ ባለቤትነትን መሰረት በማድረግ የባህር በር ባለቤትነቷን ዳግም ለማረጋገጥ እያደረገች ያለውን ጥረት በሞያቸው ለመደገፍ ዝግጁነታቸውንም አረጋግጠዋል። የባህር በር ባለቤትነት ፈጣን ምላሽ ማግኘትም ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ባለፈ ለቀጣናው ሀገራት የእርስ በርስ ትሰስርና ሰላም መጠናከር ጠቀሜታው የጎላ በመሆኑ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቱ መቀጠል አለበት ብለዋል።
በአማራ ክልል በ43 ከተሞች የኮሪደር ልማት እየተካሄደ ነው
Jun 9, 2026 189
አዲስ አበባ፤ሰኔ 2 /2018(ኢዜአ)፦የአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች በወልድያ ከተማ ሰፊ የኮሪደር ልማት ስራዎችን በምሽት ተዘዋውረው ተመልክተዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አሕመዲን መሐመድ (ዶ/ር)፤ ወልድያ በርካታ ከተሞችን የምታገናኝ በመሆኗ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቱ ስትራቴጂካዊ እሴቷን ከፍ እንዳደረገው ገልጸዋል። ቀደም ሲል የነበሩ ጎስቋላና ጠባብ ስፍራዎች ተወግደው፣ ምቹ ድልድዮችና ሰፋፊ የመዝናኛና የንግድ ቦታዎች ተከፍተዋል ነው ያሉት። ኮሪደር ልማት ከውበት የዘለለ የትውልድና የሀገር ግንባታ ጉዳይ መሆኑን ገልጸው፥ዛሬ በእነዚህ መንገዶች ላይ የሚንሸራሸሩ ህጻናት ነገ ሀገር የሚረከቡ በመሆናቸው ስራው ትውልድ ተሻጋሪ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል። የክልሉ ከተሞች ከወልድያ የፈጠራና የሀብት ቁጠባ ተሞክሮ ሊማሩ እንደሚገባ ተናግረዋል። የአማራ ክልል የከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአሁኑ ወቅት በክልሉ በሚገኙ 43 ከተሞች ውስጥ ማዘጋጃ ቤቶችን ጨምሮ የኮሪደር ልማት እንቅስቃሴ በስፋት እየተካሄደ ይገኛል። የክልሉ ከተሞች ከጎስቋላ ገፅታ ተላቀው ምቹ የሥራ፣ የመኖሪያና የቱሪዝም ሥፍራ እየሆኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ወልድያ ከተማ በከፍተኛ ፍጥነትና በጥራት በመስራት አስደናቂ ለውጥ ማምጣቷን ገልጸዋል። የከተማዋን ልማት ውስን ሀብትን በቁጠባና በጥራት የመጠቀምና ብዙ ሥራዎችን በፍጥነት የማሳካት ጥበብ በመከተል የመደመር መንግሥት ኢንተርፕረኒያል እሳቤን እየተገበረች መሆኑ ልዩ እንደሚያደርገው አብራርተዋል። የወልድያ አመራርና ህዝብ ከተማችን ተጎሳቁላ አትኖርም በሚል የጋራ መግባባት ፈጥረው፣ ሀብት አሰባስበውና ፈጣን እርምጃ ወስደው የከተማዋን የኢኮኖሚ እሴት ከፍ ማድረጋቸውን ጠቁመዋል። ይህም አመራር ከሕዝብ ጋር ተቀናጅቶ ከሠራ ማንኛውንም ተግዳሮት ማሸነፍ እንደሚቻል ትልቅ ማረጋገጫና ለክልሉም ትምህርት የሚሰጥ ነው ብለዋል።
በአርባ ምንጭ የቱሪስት መዳረሻዎችን ከጎበኙ ቱሪስቶች ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ተገኘ
Jun 9, 2026 129
አርባ ምንጭ፤ ሰኔ 2/2018 (ኢዜአ)፡-በአርባ ምንጭ ከተማና አካባቢው ያሉ የቱሪስት መዳረሻዎችን ከጎበኙ የሀገር ወስጥና የውጭ ቱሪስቶች ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን የከተማው ቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ። ከተማዋን የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከል ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራትም ውጤት መመዝገቡ ተመላክቷል። የአርባ ምንጭ ከተማ ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ አቶ ደስታ ደምበላ ለኢዜአ እንደተናገሩት በከተማው አርባ ምንጮች፣ ዓባያና ጫሞ ሐቆችን፣ የነጭ ሣር ብሔራዊ ፓርክ፣ አዞ ራንችና ሌሎች መዳረሻዎች በስፋት ይገኛሉ። ቱሪስቶች የሚያርፉባቸው ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ሪዞርቶች፣ ሎጆችና ሆቴሎች መኖራቸውን የጠቀሱት አቶ ደስታ በበጀት ዓመቱ ብቻ አራት ዓለም አቀፍ ሆቴሎች ተገንብተው ለአገልግሎት በቅተዋል። በበጀት ዓመቱ እስካሁን ድረስ ከ320 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶች ከተማዋን እንደጎበኙና ከዚህም ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ተናግረዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ ተጨማሪ የቱሪስት መዳረሻዎች እየለሙ መሆናቸው ገልጸው፣ በዚህም ከጋሞ ልማት ማህበር ጋር በመቀናጀት የተከናወኑ ተግባራት ከተማዋን የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከል እያደረጋት ይገኛል ብለዋል። የጋሞ ልማት ማህበር ዋና ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ማንደፍሮት ዱባለ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንደገለጹት ልማት ማህበሩ በበጀት ዓመቱ በዓባያ ሐይቅ ላይ የሚገኙ 11 ደሴቶችን የሚያስተሳስር የጀልባ ትራንስፖርት አገልግሎት ጀምሯል። በከተማው ግርጌ በአንድ ስፍራ የሚገኙ 40ዎቹ ምንጮችን ለመመልከት ለሚመጡ ቱሪስቶች ምቹ ሁኔታ ለመፍጠርም "አርባ ፤ አርባ ሁለት" የተሰኘ 1ሺህ 680 ደረጃ ያለው መንገድ መገንባቱን ገልጸዋል። ለጉብኝት ወደ አርባ ምንጭ ከተማ ከመጡ ቱሪስቶች መካከል ከአዲስ አበባ እንደመጣ የተናገረው ወጣት ታደለ ግዛት በከተማዋ የተለያዩ መዳረሻዎችን መጎብኘቱን ተናግሯል። አርባ ምንጭን ጨምሮ በሀገራችን ሊጎበኙ የሚገባቸው ታሪካዊ፣ ተፈጥሯዊና ባህላዊ ሀብቶች እንዳሉ ገልጾ፣ ኢትዮጵያውያን እነዚህን የቱሪዝም ሀብቶች የመጎብኘትና የማወቅ ባህል ልናዳብር ይገባል ብሏል። አርባ ምንጭና አካባቢዋ ልዩ የተፈጥሮ ሀብት የተቸረ በመሆኑ ቀልብን ይማርካል ያለው ደግሞ ከፖላንድ የመጣው ጎብኚ ሚስተር ባርተክ ሮማን ነው። በአርባ ምንጭና አካባቢው የሚገኙ 40 ዎቹ ምንጮች፣ ነጭ ሣር ብሔራዊ ፓርክ እንዲሁም ዓባያና ጫሞ ሐይቆችን በመመልከት መደሰቱን ገልጿል።