ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በዞኑ ለመጪው መኸር ሰብል ልማት የሚውል የአፈር ማዳበሪያ እየተሰራጨ ነው
Apr 21, 2026 29
ደሴ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን ለመጪው የመኸር ሰብል ልማት የሚውል ከ300 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ በማስገባት ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ለ2018/19 የመኸር ሰብል ልማት ተገቢውን ግብዓት በማቅረብ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው። በዚህም ለመጪው ምርት ዘመን ከ644 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ለማቅረብ ታቅዶ በተደረገ ጥረት እስካሁን ከ300 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ማስገባት መቻሉን ገልጸዋል።   ወደ ዞኑ ከገባው ውስጥም ከ100 ሺህ ኩንታል በላይ ወደ ወረዳዎች በማድረስ ቅድሚያ ለሚዘሩትና ሩቅ አካባቢ ለሚገኙ አርሶ አደሮች እየተሰራጨ ነው ብለዋል። ቀደም ብሎ ማዳበሪያው መሰራጨቱ አርሶ አደሩ ተረጋግቶ የዘር ሥራውን በወቅቱ ከማከናወን ባለፈ ምርታማነቱን ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥርም አስረድተዋል። በአልብኮ ወረዳ የ014 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አብዱ እንድሪስ በሰጡት አስተያየት፣ ለቀጣይ የመኸር እርሻ ከሚያስፈልጋቸው እስካሁን 3 ኩንታል ማዳበሪያ ማግኘታቸውን ገልጸዋል።   በዘንድሮው የመኸር ዘመን ሁለት ሄክታር ማሳቸውን በተለያየ ሰብል ለማልማት እየተዘጋጁ መሆኑን ጠቁመው ማዳበሪያው ቀድሞ በእጃችን መግባቱ ያለስጋት የእርሻ ስራችንን ለማከናወን ያግዘናል ብለዋል። በደቡብ ወሎ ዞን በ2018/19 የምርት ዘመን ከ432 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከ16 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያሳያል።
የልማት ዕቅድ ማስፈጸሚያ ኢንሼቲቮችን በመለየት መተግበር:-
Apr 21, 2026 51
  ‎ከ100 ቀናት ሪፖርት እና ከ9 ወራት የሥራ አፈፃፀም የተገኙ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት፤ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ ሥር የተቀረጹት ስድስት ታላላቅ ውጥኖች በመላ ሀገሪቱ የሚታይ ለውጥ እያመጡ ይገኛሉ። ‎• አረንጓዴ ዐሻራ፦ የሀገሪቱ የደን ሽፋን 23.6% ደርሷል። በዚህም የአርሶ አደሮች ገቢ እያደገ፣ አረንጓዴ የሥራ ዕድሎች እየተፈጠሩ፣ የአፈርና የውሃ ጥበቃ ሥራዎች እየተከናወኑ እንዲሁም ሥነ-ምህዳሩ ከመቼውም ጊዜ በላይ ጤናማ እየሆነ መጥቷል። ‎‎• ሀገራዊ የስንዴ ልማት፦ ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን እና ሉዓላዊነትን እያረጋገጠች ትገኛለች። አዳዲስ የግብርና ዕውቀቶች እየተስፋፉ፣ የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎች ግብዓቶችን እያገኙ፣ ውድ የሆኑ የውጭ ምርቶች በሀገር ውስጥ እየተተኩ፣ የሥራ ዕድሎች እየሰፉና የአርሶ አደሮች ገቢ እየጨመረ ይገኛል። ‎‎• የሌማት ትሩፋት፦ የግብርና ግብዓቶች አቅርቦት እና ምርታማነት እየጨመረ ነው። የተመጣጠነ ምግብ በቀላሉና በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲገኝ ከማድረግ ባለፈ፣ አነስተኛ የንግድ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡና አካባቢው ይበልጥ እንዲጠበቅ እያደረገ ይገኛል። ‎‎• ዲጂታል ኢትዮጵያ፦ የሕግ፣ የፋይናንስ እና የማንነት መታወቂያ (ID) ሥርዓቶች ወደ ዲጂታል እየተቀየሩ ነው። የኢንተርኔት ተደራሽነትና የኦንላይን አገልግሎቶች እየተስፋፉ፣ የሞባይል ክፍያ ሥርዓት እየተጠናከረ እንዲሁም የኢ-ኮሜርስ ንግድ የዜጎችን ጊዜና ገንዘብ እያተረፈ ነው። ‎‎• የከተማና የገጠር ኮሪደር ልማት፦ የከተሞች መሠረተ ልማት በአረንጓዴ ትራንስፖርት እየዘመነ ነው። ይህም የዜጎችን የኑሮ ጥራት እያሻሻለ፣ የአካባቢ ንግድን እያነቃቃ እንዲሁም በከተማና በገጠር መካከል ያለውን ትስስር እያጠናከረ ይገኛል። ‎‎• ኢትዮጵያ ታምርት፦ የማምረት አቅምና የምርቶች እሴት የመጨመር ሂደት እየተሻሻለ ነው። ከውጭ የሚገቡ ምርቶች በሀገር ውስጥ እየተተኩ፣ የውጭ ምንዛሬ ግኝት እያደገ፣ የግብዓት አቅርቦት እየተጠናከረና አዳዲስ የሥራ ዕድሎች እየተፈጠሩ ነው። ‎‎እያንዳንዱ ምሰሶ ፈተናዎችን ወደ መልካም አጋጣሚ በመቀየር፣ ጠንካራ እና ራሷን የቻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት ጉልህ ሚና እየተጫወተ ነው። #PMOEthiopia
ኢትዮጵያ እና ፈረንሳይ የኢኮኖሚ አጋርነታቸውን ያጠናክራሉ
Apr 21, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና ፈረንሳይ በኢኮኖሚ ዘርፍ ላይ ያላቸውን አጋርነት ለማጠናከር ተስማምተዋል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) የፀደይ ስብሰባ ጎን ለጎን በዋሽንግተን ዲሲ ከፈረንሳይ ግምጃ ቤት ከፍተኛ ኃላፊዎች ጋር ተወያይተዋል። ውይይቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የሁለትዮሽ የልማት ትብብር ይበልጥ ማሳደግ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ያተኮረ እንደነበርም ተመላክቷል።   ፈረንሳይ የመንግሥታት አበዳሪዎች ኮሚቴን በሊቀ መንበርነት በመራችበት ወቅት በኢትዮጵያ የዕዳ ሽግሽግ ሂደት ላይ ላበረከተችው አስተዋጽኦም ሚኒስትር አህመድ ሽዴ አመስግነዋል። ሁለቱ ሀገራት በኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እና በዕዳ መልሶ ማዋቀር ሂደት ላይ በጋራ ለመስራት ቁርጠኛ መሆናቸውንም አስታውቀዋል። ይህም አዳዲስ የፋይናንስ ፍሰቶችን ለማምጣትና ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ኢዜአ ከገንዘብ ሚኒስቴር ያገኘው መረጃ ያመላክታል።
የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም ድጋፉን እንደሚያጠናክር ገለጸ
Apr 20, 2026 708
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ ለሚከናወኑ የኢኮኖሚ ሪፎርም ስራዎች ያለውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋገጠ። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት እና የዓለም ባንክ የፀደይ ወቅት ስብሰባ በዋሺንግተን ዲሲ ተካሄዷል። በገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ የተመራ ከፍተኛ ልዑክ ከስብሰባው ጎን ለጎን ከዓለም ባንክ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ፓስካል ዶኖሆ ጋር ውይይት አድርጓል። ሚኒስትሩ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ (Homegrown Economic Reform Agenda) የተመዘገቡ ውጤቶችን ያብራሩ ሲሆን፤ በተለይም በኢኮኖሚ መረጋጋትና በመዋቅራዊ ሽግግር ረገድ የተመዘገቡ ስኬቶችን አንስተዋል።   ኢትዮጵያ ወደ ግል ዘርፍ መር የኢኮኖሚ እድገት በምታደርገው ሽግግር፣ የግል ካፒታልን ማሰባሰብ አሁን ላይ ዋነኛው ትኩረት መሆኑን ሚኒስትሩ አፅንኦት የሰጡት ጉዳይ ነው። በተጨማሪም ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት (COP32) ጉባኤን ለማስተናገድ እያደረገችው ስላለው ዝግጅት ለዳይሬክተሩ ገለጻ አድርገዋል። ጉባኤው የኢትዮጵያን የአየር ንብረት መቋቋም አቅምና የአረንጓዴ ልማት ቃል ኪዳኖችን እውን ለማድረግ ያለውን ጉልህ ፋይዳ ጠቁመዋል። የዓለሞ ባንክ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ፓስካል ዶኖሆ በበኩላቸው የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የኢኮኖሚ ማሻሻያ እርምጃዎቹ ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የሚያደርጋቸውን ድጋፎች ለማሳደግ ቁርጠኛ መሆኑንም አመልክተዋል። ዳይሬክተሩ ለኢትዮጵያ የኮፕ 32 ጉባኤ ዝግጅትም ድጋፍ ለማድረግ ቃል የገቡ ሲሆን፣ በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት ለማድረግ ዝግጁ እንደሆኑ መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል። Boost this post to get more reach for Ethiopian News
በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተከናወኑ ተግባራት ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ ናቸው
Apr 20, 2026 304
ቦንጋ ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ህብረተሰቡንና የልማት አጋሮችን በማሳተፍ የተከናወኑት ተግባራት ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ መሆናቸውን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ። በክልሉ የመንግስትና የፓርቲ የዘጠኝ ወራት የስራ አፈፃፀም ግምገማ መድረክ በቦንጋ ከተማ ተካሂዷል ።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በመድረኩ ማጠቃለያ ላይ እንደገለጹት፤ በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ህብረተሰቡንና የልማት አጋሮችን በማሳተፍ የተከናወኑት ተግባራት ለህዝብ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ ናቸው። በመሰረተ ልማት፣ በገቢ አሰባሰብ፣ በግብርና፣ በስራ እድል ፈጠራ ፣ በጤና፣ በትምህርትና በሌሎችም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰዋል። በክልሉ የተመዘገቡ ልማቶች አበረታች ቢሆኑም ከክልሉ የመልማት አቅም አንፃር ገና ሰፊ ስራ የሚጠይቅ በመሆኑ ይበልጥ መትጋት እንደሚገባ ገልጸዋል። ለዚህም የክልሉን አመራሮችና ሰራተኞች እስከታችኛው መዋቅር ድረስ በማቀናጀት ተከታታይነት ያለው ድጋፍና ክትትል ማድረግ እንደሚገባም አክለዋል። ባለፉት ዘጠኝ ወራት በመንግስትም ሆነ በፓርቲ የተመዘገቡ ውጤቶችን ማስቀጠል ይገባል ያሉት ደግሞ የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ፍቅሬ አማን ናቸው።   በተለይም አመራሩ ስራን በመገምገምና በቅንጅት በመስራት እንዲሁም ህብረተሰቡን በማስተባበር የመጡ ውጤቶችን ማስቀጠል እንዳለበት አስገንዝበዋል።
ኢትዮጵያ የፖሊሲ እርምጃዎችን በመውሰድ ዋነኛ የኢንቨስትመንት መዳረሻ እየሆነች ነው
Apr 20, 2026 498
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ንግድና ኢንቨስትመንትን የሚያጠናክሩ የፖሊሲ እርምጃዎችን በመውሰድ ዋነኛ የኢንቨስትመንት መዳረሻ እየሆነች ነው ሲሉ የአውሮፓ ሕብረት የዓለም አቀፍ ትብብር ኮሚሽነር ጆዜፍ ሲከላ ገለጹ። የአውሮፓ ሕብረት እና ኢትዮጵያ የቢዝነስ ፎረም "ዓለም አቀፍ የገበያ መግቢያ አቅምን መጠቀም" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። የአውሮፓ ሕብረት ዓለም አቀፍ ትብብር ኮሚሽነር ጆዜፍ ሲከላ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት መስራች፣ የቡና መገኛ፣ ለኢንቨስትመንት ምቹ የሆነች ታሪካዊ ሀገር ናት።   ኢትዮጵያ ንግድና ኢንቨስትመንትን የሚያጠናክሩ የፖሊሲ እርምጃዎችን በመውሰድ መዳረሻዋ የት እንደሆነ በግልጽ አሳይታለች ብለዋል። የአውሮፓ ሕብረት ደረጃቸውን የጠበቁ የመሰረት ልማትና የዲጂታል መሰረተ ልማት ይፈልጋል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ሕብረቱ በገጠር መሰረተ ልማት ግንባታ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። የአውሮፓ ሕብረት እና ኢትዮጵያ ቢዝነስ ፎረም በንግድ ድርጅቶች መካከል፣ በመንግሥት እና በንግድ ድርጅቶች መካከል ገንቢ ውይይት ማድረግ እንደሚያስችል ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጣ የኢኮኖሚ ሪፎርም ማድረጓንም ኮሚሽነሩ ገልጸዋል። ዛሬ ከአውሮፓ ህብረት ጋር ከበጀት ድጋፍ ስምምነቱ ባሻገር የ150 ሚሊዮን ዩሮ የዲጂታል ኢኮኖሚ ስምምነት መፈረሙን ገልጸዋል፡፡ ይህም በዲጂታል መሰረተ ልማት፣ ክህሎትና አስተዳደር በጋራ ማዕቀፍ ላይ የተመሰረተ መሆኑን አብራርተዋል።   የአፍሪካ አሕጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ዋና ጸሀፊ ዋምኬሌ ሜኔ፤ አፍሪካ ከአራት ሺህ በላይ የአውሮፓ ኩባንያዎች በመሳተፍ በዓለም ቀዳሚዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህ ትብብር በአፍሪካ አሕጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸው፤ የተበጣጠሰ የእሴት ሰንሰለት ባለው የዓለም ገበያ በአፍሪካ የበለጠ ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለዋል። ኢትዮጵያ የቢዝነስ ስራዎችን የሚያቀላጥፉ የጉምሩክና የፋይናንስ ስርዓቷን እያዘመነች መሆኑን ጠቅሰው፤ የዲጂታል ክፍያ ስርዓት መፈጠሩን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ትርጉም ያለው ሪፎርም በማድረግ ሀገሪቷን በአፍሪካ ባለ ግዙፍ ኢኮኖሚ ባለቤት አድርጓታል ብለዋል። የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም ቁልፍ የፋይናንስ ተቋማትን አቅም በማጠናከር የተሳለጠ የንግድና ኢንቨስትመንት ፍሰት እንዲኖር ያስችላል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዘመናዊ አሰራሮችን በመተግበር በሀገር ግንባታ ሂደት የበኩሉን እየተወጣ ነው
Apr 20, 2026 271
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዘመናዊ አሰራሮችን በመተግበር በሀገር ግንባታ ሂደት የበኩሉን እየተወጣ እንደሚገኝ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ የትምጌታ አስራት (ዶ/ር) አመለከቱ፡፡ የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋር በመተባበር ባዘጋጀው የ75ኛ ዓመት የአልማዝ እዮቤልዩ በዓል መክፈቻ ሥነ ሥርዓት በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ተካሂዷል።   አስተዳደሩ ከምስረታው ጀምሮ አሁን የደረሰበትን ልህቀት ስኬቶችና ተሞክሮዎችን የሚያስቃኝ አውደ ርዕይም በማዕከሉ ተከፍቷል። የተለያዩ ከያኒያንም በዓሉን በማስመልከት ልዩ ልዩ የኪነ ጥበብ ሥራዎችን አቅርበዋል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ የትምጌታ አስራት (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ አስተዳደሩ በሀገር ግንባታ ሂደት በአርዓያነት የሚጠቀስ አስተዋጽኦ አበርክቷል። በተቋም ግንባታ በኩልም አስተዳደሩ ምሳሌ የሚሆን ተግባራትን አከናውኗል ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ለዘርፉ ዕድገት ጠንካራ የግል ተቋራጭና አማካሪዎች እንዲፈጠሩ የማይተካ ሚና መጫወቱን ተናግረዋል።   የዘርፉን ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉ ባለሙያዎችም እንዲበቁ በማድረግ ረገድ ተቋሙ ያከናወናቸው ተግባራትም በትውልድ ቅብብሎሽ ሀገር የመገንባት ሂደቱን ውጤታማ በሆነ መሰረት ላይ እንዲቀመጥ አስችሏል ብለዋል። አስተዳደሩ በቀጣይም ዘመኑን የዋጁ አሰራሮች በመከተልና ጥናትና ምርምሮችን መሰረት በማድረግ ለላቀ ውጤት ሊተጋ እንደሚገባም አመልክተዋል። የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መሀመድ አብዱራህማን በበኩላቸው፤ አስተዳደሩ ዘመኑን የዋጁ አሰራሮችን በመከተል ብልፅግናን የሚያረጋግጡ ወጤታማ ተግባራትን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   ለውጤት የበቁ ዘመናዊ የፍጥነት መንገዶች፣ የተለያዩ ድልድዮች እንዲሁም ተቋሙ የተከተላቸው የዲጂታል ቴክኖሎጂ አጠቃቀሞች ለስኬቱ ማሳያዎች ናቸው ብለዋል። የአልማዝ እዮቤልዩ በዓሉ የተሻለች እና ዘመናዊ ኢትዮጵያን ለመገንባት ቃላችንን የምናድስበት ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የምህንድስናን ጥበብ ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር በማቀናጀት የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። አስተዳደሩ ጥናትና ምርምርን ማዕከል ያደረጉ ሥራዎችንም በሰፊው ገቢራዊ እንደሚያደርግም ጠቁመዋል።
ሀኪም ጋራ ኢኒሼቲቭን በጥራትና በፍጥነት ለማጠናቀቅ ይሰራል - አቶ ኦርዲን በድሪ
Apr 20, 2026 100
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ) ፦ በሀረር ከተማ የተጀመረውን ሀኪም ጋራ ኢኒሼቲቭ በጥራትና ፍጥነት ለማጠናቀቅ እንደሚሰራ የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ገለፁ። ርዕሰ መስተዳድሩና ካቢኔያቸው በክልሉ እየተገነባ የሚገኘው የሀኪም ጋራ ኢኒሼቲቭን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።   በዚህ ወቅትም ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት በአው ሀኪም ተራራ ላይ እየተሰራ የሚገኘው ኢኒሼቲቩ የአዲሲቷ ሀረር አለም አቀፍ ምልክት ከመሆን ባሻገር ለክልሉ የቱሪዝም ዘርፍ እድገት ጉልህ አስተዋጽኦ ይኖረዋል። ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅም ለቱሪዝም መዳረሻነትና ለህዝብ መዝናኛነት አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል። ከዚህ በተጨማሪም የፕሮጀክቱ እውን መሆን የጎብኚዎች ቆይታን በመጨመር ተጠቃሚነትን ከማሳደግ አንፃርም ሚናው ከፍ ያለ መሆኑን ተናግረዋል።   በፕሮጀክቱም 1ሺህ 870 ደረጃዎች እና 2 ኪሎሜትር የሚጠጋ የመሰረተ ልማት ስራ እንደሚከናወን የገለፁት ርዕሰ መስተዳድሩ ፕሮጀክቱ አካባቢያዊ ሀብቶችን በመጠቀም ይሰራል ብለዋል። ተራራው ራሱን የቻለ የህግ ማዕቀፍ እንዲኖረው በማድረግ ተገቢው ጥበቃ እንደሚደረግለት አመላክተው ለዚህም ህገ-ወጥ ግንባታን በመከላከል ረገድ በቅንጅት እንደሚሰራም ተናግረዋል። ፕሮጀክቱን በተያዘለት ጊዜና ጥራት ለማጠናቀቅ እንደሚሰራ ጠቁመው ለዚህም የተጠናከረ ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል ሲሉ ነው የተናገሩት።
በክልሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በኢኮኖሚ ዘርፍ በተከናወኑ ስራዎች አበረታች ውጤት ተመዝግቧል
Apr 20, 2026 84
ቦንጋ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ባለፉት ዘጠኝ ወራት በኢኮኖሚ ዘርፍ በተከናወኑ ስራዎች አበረታች ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ገለጸ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የመንግስትና የፓርቲ የዘጠኝ ወራት የስራ አፈፃፀም ግምገማ መድረክ በቦንጋ ከተማ እየተካሄደ ነው።   በመድረኩ የክልሉን መንግስት የስራ እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ያቀረቡት የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ሀላፊ ወሰነች ቶማስ እንደገለፁት፤ በበጀት ዓመቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በዋና ዋና የኢኮኖሚ ዘርፎች አበረታች ውጤት ተመዝግቧል፡፡ በተለይም የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰጠው ትኩረት በ2017/18 ምርት ዘመን በመኽር ወቅት 23 ሚሊዮን ኩንታል የሰብል ምርት መሰብሰቡን አንስተው በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ደግሞ እስካሁን 154 ሺህ 279 ኩንታል ምርት መሰብሰቡን ለአብነት ጠቅሰዋል። በክልሉ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ በተከናወነው ተግባር በግብርና፣ በአገልግሎትና በኢንዱስትሪ ዘርፎች 5 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ 93 አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች ፈቃድ መሰጠቱንም አመልክተዋል። በተለያዩ ዘርፎች ለ57 ሺህ ዜጎች የስራ ዕድል መፈጠሩንና ከተቋማት ጋር በመተባበር ከ658 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር መመቻቸቱን አንስተዋል።   ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተከናወኑ ኢኮኖሚያዊ ተግባራት የመንግስትንና የህዝብን ቅንጅት ያሳዩ መሆናቸውን ያነሱት ደግሞ የመድረኩ ተሳታፊና የክልሉ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ህዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አክሊሉ ወልደሚካኤል ናቸው። ተግባሩን ለማላቅም በቀሪ ጊዜያት የተጀመሩ ስራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል ብለዋል። የክልሉ ጤና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኢብራሂም ተማም በበኩላቸው፤ ከመሠረተ ልማት አንፃር እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች መልካም መሆናቸውን ጠቁመው በቀጣይም ቅድሚያ ሊሰጣቸው የሚገቡትን ለይቶ ትኩረት በመስጠት የተጀመሩ ስራዎች እንዲጠናከሩ ማድረግ ይገባል ብለዋል። በመድረኩ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)፣ በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ፍቅሬ አማንን ጨምሮ ሌሎች የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እየተሳተፉ ነው።
በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ለሚሰማሩ የአውሮፓ ሕብረትና አባል ሀገራት ኩባንያዎች መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል
Apr 20, 2026 335
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ለሚሰማሩ የአውሮፓ ሕብረትና አባል ሀገራት ኩባንያዎች መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው ገለጹ፡፡ የአውሮፓ ሕብረት እና ኢትዮጵያ የቢዝነስ ፎረም "ዓለም አቀፍ የገበያ መግቢያ አቅምን መጠቀም" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው።   የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት ዘላቂ ዕድገት ማስመዝገብ የሚያስችል ሁሉን አቀፍ ሪፎርም አድርጋለች። ኢትዮጵያ አካታችና ሁሉን አቀፍ ሪፎርም በማድረግ ያላትን ዕምቅ አቅም መጠቀም የሚያስችል ለውጥ እያመጣች መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያና የአውሮፓ ሕብረት ቢዝነስ ፎረም ኢትዮጵያ ያላትን አቅም ለማውጣት፣ ትብብርን ለመፍጠር፣ የገበያ አማራጮችን ለማሰስ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ የግሉን ዘርፍ በማጠናከር ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንትን መሳብ መቻሉንም ገልጸዋል፡፡ ከሪፎርሙ በኋላ የውጭ ምንዛሪ ክምችት ጨምሯል፤ የዋጋ ግሽበት ቀንሷል፤ ከወጪ ንግድ የሚገኘው የምንዛሪ መጠን በእጅጉ አድጓልም ብለዋል። ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም በተያዘው ዓመት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ 9 ነጥብ 2 በመቶ እድገት እንደሚያስመዘገብ መተንበዩን በመጥቀስ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ አሕጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናን በመተግበር ምቹ የኢንቨስትመንት መዳረሻነቷን እያጠናከረች መሆኑን ገልጸዋል።   መንግሥት የግሉን ዘርፍ ተሳትፎና የዲጂታል ግብይትን ማጠናከር የሚያስችል የዲጂታል ክፍያና አገልግሎት ስርዓት ማዘመኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በብዝሀ የኢንቨስትመንት ዘርፍ ተመራጭ መሆኗን በመጥቀስ፣ የአውሮፓ ሕብረትና አባል ሀገራት ኩባንያዎች በኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ በታዳሽ ሀይል፣ ቴክኖሎጂ፣ ጋርመንትና መሰል ዘርፎች መሰማራት ይችላሉ ብለዋል። ለኢንቨስትመንት ምቹ ሥነ ምህዳርና መሰረተ ልማት በመዘርጋት ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። የአውሮፓ ሕብረትና አባል ሀገራት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው መዋዕለ ንዋያቸውን ማፍሰስ እንደሚችሉ ገልጸው፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ለኢንቨስተሮች አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ ነው ብለዋል። የኦስትሪያ ሪፐብሊክ የአውሮፓና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ሚኒስትር ቤአተ ማይነል ረይዚንገር ፤የዓለም ነባራዊ ሁኔታ ጠንካራ የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር የሚፈጠርበት ወቅት መሆኑን ገልጸዋል፡፡   የዓለም ጂኦፖለቲካና ፖሊቲካዊ ሁኔታ ፈታኝ መሆኑን ገልጸው፤ ኦስትሪያ የዓለምን ንግድና ኢንቨስትመንት በር ክፍት ለማድረግ በሚደረገው ጥረት አጋር ለመሆን ዝግጁ ናት ብለዋል፡፡ በኦስትሪያ የኢንዱስትሪ አቅሞችን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለማሳደግ እየሰራን ነው ያሉት ሚኒስትሯ፤ ከጣሊያን ጋር በመተባበር ለአየር ንብረት ለውጥ በማይበገር የቡና ምርት የዓለም አቀፍ መግቢያ ፕሮጀክት እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ በዓለም ልዩ የሆነ የቡና ሥርዓት ዝግጅት እንዳላት ገልጸው፤ በኢ-ተገማች የዓለም ነባራዊ ሁኔታ ከአጋራ አካላት ጋር ትብብርን ማጠናከር ይገባል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ተስፋ ያላት ሀገር ናት ያሉት ሚኒስትሯ፤ የኦስትሪያና አውሮፓ ህብረት ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ዘርፍ ለመሰማራት ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኮንስትራክሽን ዘርፉ መነቃቃት ትልቅ ዕድል ፈጥሯል
Apr 20, 2026 159
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የግንባታ ግብዓትን በሀገር ውስጥ በመተካት ለኮንስትራክሽን ዘርፉ መነቃቃት ትልቅ ዕድል መፍጠሩን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ገለጹ። በሀገር አቀፍ ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ የተዘጋጀው የኢትዮጵያ የመሠረተ ልማትና ኮንስትራክሽን ሣምንት መርሃ ግብር በአዲስ ዓለምአቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ተካሂዷል። በዚህም "የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በመሠረተ ልማት እና በኮንስትራክሽን" በሚል ርዕስ የፓናል ውይይት ተካሂዷል።   የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተተገበረ የሚገኘው ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኮንስትራክሽን ዘርፉ መነቃቃት ትልቅ ዕድል ፈጥሯል። በኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ዘርፍ ያለውን እምቅ አቅም በአግባቡ ለመጠቀም ንቅናቄው ከውጭ የሚገቡ የግንባታ ግብዓት በሀገር ውስጥ የመተካት ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በዘርፉ ያለውን ከፍተኛ ፍላጎትና ዕድል ወደ ተግባር ለመለወጥ መንግሥት ቁርጠኛ መሆኑንም አብራርተዋል። ይህ ንቅናቄ የሀገርን ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ በማዋል የውጭ ምንዛሬን የሚታደጉ የኢንዱስትሪ ውጤቶችን በአገር ውስጥ ለማምረት እያስቻለ መሆኑን ገልፀዋል። የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር ሮቤል ፀጋዬ፣ የኮንስትራክሽን ዘርፉን ከውጭ ጥገኝነት ለማላቀቅ ግብዓቶችን በሀገር ውስጥ የማምረት ስትራቴጂያዊ ለውጥ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ገልፀዋል።   ኮርፖሬሽኑ መግዛት ብቻ ሳይሆን መገንባት የሚል አዲስ መርህ በመከተል ግብዓቶችን ከመግዛት ይልቅ በሀገር ውስጥ ወደ ማምረት መሸጋገር መቻሉን ጠቅሰዋል። በውጭ አቅራቢዎች ላይ ያለን ጥገኝነት በመቀነስ የገበያ ቁጥጥርን ማሳደግ እና የተበታተኑ የግንባታ ሂደቶችን ወደተቀናጀ ሥርዓት ማምጣት ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ይህ የሽግግር ጉዞ የኮንስትራክሽን ዘርፉን ለሀገር ግንባታ ያለውን አስተዋጽኦ ይበልጥ የሚያጠናክርና ኢትዮጵያን በዘርፉ ራሷን እንድትችል የሚያደርግ መሆኑን ገልፀዋል። የማዕድን ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብስራት ከበደ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የማዕድን ሀብት በመጠቀም በኮንስትራክሽን ዘርፉ የሚታየውን የገቢ ምርት ጥገኝነት ለመቅረፍ ስልታዊ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል።   በኢትዮጵያ ለሲሚንቶ፣ ለብረት፣ ለሴራሚክስ፣ ለመስታወት እና ለጌጣጌጥ ድንጋዮች ኢንዱስትሪዎች ግብዓት የሚሆኑ እንደ ብረት ማዕድን፣ ማርብል፣ ግራናይት፣ ድንጋይ ኖራ፣ ጂፕሰም እና ሲሊካ-ሳንድ ያሉ እጅግ ከፍተኛና ጥቅም ላይ ያልዋሉ የማዕድን ክምችቶች እንዳሉ ጠቅሰዋል። እነዚህን ሀብቶች ማልማት የኢንዱስትሪ ዕድገትን ከማፋጠኑ ባለፈ፣ የውጭ ምንዛሬን ለማዳንና ሰፊ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። የኮንስትራክሽን ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ታምራት ሙሉ እንደገለፁት፤ ጥራት ያላቸው የኮንስትራክሽን ግብዓቶችን በሀገር ውስጥ ማምረት እንዲቻል ኢንስቲትዩቱ የበኩሉን እየተወጣ ነው።   የፖሊሲ ድጋፍን ጨምሮ የጥራት መስፈርቶችን በማዘጋጀት የተለያዩ ድጋፎችን እያደረገ እንደሚገኝም ተናግረዋል።
የኮንስትራክሽን ዘርፍ የልህቀት ማዕከል ግንባታ እየተከናወነ ነው
Apr 20, 2026 159
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፡- የኮንስትራክሽን ዘርፍ እድገትን ይበልጥ በሳይንሳዊ መንገድ ለመምራት የሚያስችል የልህቀት ማዕከል ግንባታ እየተከናወነ መሆኑ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ የትምጌታ አስራት (ዶ/ር) ገለፁ። በሀገር አቀፍ ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ የተዘጋጀው የኢትዮጵያ የመሠረተ ልማትና ኮንስትራክሽን ሣምንት መርሃ ግብር በአዲስ ዓለምአቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ተካሂዷል። በዚህም "የግንባታ ኢንዱስትሪ ትራንስፎርሜሽን ኢኒሼቲቭ" በሚል ርዕስ የፓናል ውይይት ተካሂዷል።   የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ የትምጌታ አስራት (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት የመንገዶች፣ ድልድዮችንና የግድቦች ግንባታን በስፋት እያከናወነች ትገኛለች። ይህም ሀገሪቱ በግንባታ ሂደት ላይ መሆኗን የሚያመላክት ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ እኛ ስንገነባ ሀገር ትገነባለች በሚል እሳቤ በእያንዳንዱ እንቅስቃሴ ውስጥ መሠረተ ልማትን በማስፋፋት የኢትዮጵያን ብልፅግና የማረጋገጥ ሥራ እየተሰራ መሆኑን አስገንዝበዋል። በግንባታው ሂደት የሚሳተፉ የሀገር ውስጥ የሥራ ተቋራጮችና ኩባንያዎች አቅማቸውን በማሳደግ በሀገር ውስጥ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ መሆን አለባቸው ብለዋል። ለዚህም ይረዳ ዘንድ ዘርፉን ዘመናዊ፣ ውጤታማና ተወዳዳሪ ማድረግ፣ ጠንካራ ቁጥጥርና ክትትል ሥርዓት መዘርጋት እና ተቋማዊ የአቅም ግንባታ ሥራዎችን ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑ ተናግረዋል። የዘርፉን ዕድገት በሳይንሳዊ መንገድ ለመምራት የልህቀት ማዕከል ግንባታ እየተከናወነ መሆኑ ገልፀዋል። በግንባታው ዘርፍ የሚታዩ ችግሮችን ለመቅረፍና ውጤታማነትን ለማረጋገጥ ባለድርሻ አካላት በቅንጅት መስራት እንዳለባቸው ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መስፍን ነገዎ( ዶ/ር) በፓናል ውይይቱ ባቀረቡት ጽሁፍ ፤በኢትዮጵያ የግንባታ ኢንዱስትሪ ውስጥ የሚታዩ የአሰራር ክፍተቶችን ለመቅረፍ እና ዘርፉን ለማዘመን የተቀናጀ የቁጥጥር ማዕቀፍ እና የዲጂታል አሰራር ሥርዓት መዘርጋት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።   ዘርፉ ለሀገር ውስጥ ጠቅላላ ምርት ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ቢሆንም፣ አሁንም ድረስ የቆዩና በእጅ የሚከናወኑ አሰራሮች፣ የተበታተኑ መረጃዎች እና የግልጽነት ማነስ እንደ ዋና ተግዳሮት መቀጠላቸውን አስረድተዋል። የግንባታው ዘርፍ ወደ ተሻለ ደረጃ እንዲሸጋገር ፖሊሲዎችን፣ ሕጎችን፣ ደረጃዎችን እና ዲጂታል ቴክኖሎጂን ያጣመረ ሁሉን አቀፍ የቁጥጥር ስርዓት መዘርጋት ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ የኮንስትራክሽን ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ቅድስት ማሞ በበኩላቸው፤ የዘርፉን አቅም ለማሳደግ የሰው ኃይል ልማት፣ የቴክኖሎጂ አጠቃቀም እና ተቋማዊ አደረጃጀትን ማጠናከር ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።   የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪው በአሁኑ ወቅት ወሳኝ በሆነ የለውጥ ምዕራፍ ላይ እንዳለም ገልፀዋል።
የአፍሪካ ልማት ባንክ ለኢትዮጵያ የልማት አጀንዳዎች ያለውን አጋርነት እንደሚቀጥል ገለጸ
Apr 20, 2026 169
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ልማት ባንክ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ስትራቴጂካዊ አጋርነት በማጠናከር፣ ለሀገሪቱ የልማት የቅድሚያ ትኩረቶች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አስታወቀ። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት እና የዓለም ባንክ ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብስባ በዋሺንግተን ዲሲ ተደርጓል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ፣ ከስብሰባው ጎን ለጎን ከአፍሪካ ልማት ባንክ ፕሬዝዳንት ሲዲ ኡልድ ታህ (ዶ/ር) ጋር ውይይት አድርገዋል። ውይይቱ ሁለንተናዊ ለውጥ የሚያመጡ የልማት ትብብሮችን ማሳደግን ያለመ ነው።   በኢትዮጵያና በአፍሪካ ልማት ባንክ መካከል ያለውን ጠንካራ አጋርነት መረጋገጥ የሚያሳይ መሆኑ ተገልጿል። ባንኩ የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ሪፎርም ስራዎችና የረጅም ጊዜ የልማት ግቦችን ለማሳካት የሚጫወተው ወሳኝ ሚናም ተነስቷል። ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ተግዳሮቶች ቢኖሩም የሪፎርም አጀንዳዋን ተግባራዊ በማድረግ ቀጣይነት ያለው እድገት እያስመዘገበች መሆኑን አመልክተዋል። መንግስት ለማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋት፣ ለግሉ ዘርፍ መሪነት እና ለተቋማዊ ሽግግር በቁርጠኝነት እየሰራ ነው ብለዋል። የአፍሪካ ልማት ባንክ ፕሬዝዳንት ሲዲ ኡልድ ታህ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ በሪፎርሙ እያመጣች ያለውን ለውጥና ተለዋዋጭ ሁኔታዎችን የመቋቋም አቅም አድንቀዋል።   ባንኩ ኢትዮጵያ ቅድሚያ ለምትሰጣቸው የልማት ጉዳዮች የሚያደርገውን ጠንካራ ድጋፍ እንደሚቀጥል አመልክተዋል። ሁለቱ ወገኖች ሁሉን አቀፍ እድገትን ለማስቀጠልና የስራ እድል ፈጠራን ለማፋጠን ቁልፍ በሆኑት የኢነርጂ፣ የመሰረተ ልማት፣ የግብርና እና የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ዘርፎች ላይ ትብብራቸውን ይበልጥ ለማሳደግ ተስማምተዋል። ኢትዮጵያና የአፍሪካ ልማት ባንክ ዘላቂ የኢኮኖሚ ሽግግርን ለማምጣትና ስትራቴጂካዊ አጋርነታቸውን ለማላቅ ያላቸውን ቁርጠኝነት መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
ኢትዮጵያ እና የጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) የልማት ትብብራቸውን የበለጠ ያጠናክራሉ
Apr 20, 2026 130
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ እና የጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) የልማት ትብብራቸውን የበለጠ እንደሚያጠናክሩ አስታወቁ፡፡ በገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሺዴ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ የ2026 የዓለም ገንዘብ ድርጅትና የዓለም ባንክ የጸደይ ወቅት ስብሰባ ጎን ለጎን ከጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) ምክትል ፕሬዚዳንት ናኦኪ አንዶ ጋር ተወያይቷል፡፡ ሚኒስትሩ አህመድ ሺዴ ኢትዮጵያ ከጃፓን ብሎም ከጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) ጋር ላላት የረጅም ጊዜ ትብብር አድናቆታቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለይም በመሠረተ ልማት፣ ግብርና፣ ጤና፣ ትምህርት፣ በፋይናንስ፣ ቴክኒክ እና በአቅም ግንባታ ዘርፎች ላይ ኤጀንሲው እያደረገ ላለው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል፡፡   ሚኒስትሩ አህመድ ሺዴ ለምክትል ፕሬዚዳንቱ የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሪፎርም አጀንዳ በተመለከተም ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ጃይካ በአቪየሽን፤ በኀይል ልማት እና በመንገድ መሰረተ ልማተ ዘርፎች የሚያደርገውን ድጋፍ እንዲያጠናክር መጠየቃቸውን ኢዜአ ከገንዘብ ሚኒስቴር ያገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡ ኢትዮጵያ ለምታዘጋጀው የኮፕ 32 ጉባዔ እያደረገች ባለው ዝግጅት ላይም የተወያዩ ሲሆን ጃይካ በአየር ንብረት መቋቋምና አረንጓዴ ልማት እቅዶች ላይ እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል። የጃፓን ዓለም አቀፍ ትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) ምክትል ፕሬዚዳንት ናኦኪ አንዶ በበኩላቸው፤ ጃይካ ለኢትዮጵያ የልማት አጀንዳ የሚሰጠውን ድጋፍ እንደሚቀጥልና በተመሳሳይም ቅድሚያ በሚሰጣቸው መስኮች ላይ ትብብሩን እንደሚያጠናክር አረጋግጠዋል።
ኢትዮጵያ እና የአውሮፓ ህብረት ስትራቴጂያዊ አጋርነታቸውን ያጠናክራሉ
Apr 20, 2026 140
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና የአውሮፓ ህብረት ስትራቴጂያዊ አጋርነታቸውን እንደሚያጠናክሩ ገለጹ። በገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሺዴ የተመራ ልዑክ በዋሽንግተን ዲሲ እየተካሄደ ካለው የ2026 የዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይኤምኤፍ) እና ዓለም ባንክ የጸደይ ወቅት ስብሰባ ጎን ለጎን ከአውሮፓ ኅብረት የዓለም አቀፍ አጋርነት ኮሚሽነር ጆሴፍ ሲኬላ ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አካሂዷል። ውይይቱ በኢትዮጵያ እና በአውሮፓ ህብረት መካከል ያለውን ስትራቴጂክ አጋርነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ ያለመ መሆኑም ተገልጿል።   በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለውን ኢኮኖሚያዊ ትብብር ማሳደግ ላይ ያተኮረ እንደነበርም ኢዜአ ከገንዘብ ሚኒስቴር ያገኘው መረጃ ያመላክታል። የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለመደገፍ፣ የኢንቨስትመንት ምህዳሩን ይበልጥ ለማሻሻል፣ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም በሚያስችሉ ስራዎች እና ቀጣይነት ባለው የኢኮኖሚ እድገት ግቦች ላይ በትብብር ለመስራት አቅጣጫ መቀመጡም ተገልጿል። ኢትዮጵያ እና የአውሮፓ ህብረት የጋራ ተጠቃሚነታቸውን በሚያረጋግጥ መልኩ ትብብራቸውን ለማጠናከር ቁርጠኝነታቸውን ማረጋገጣቸውም ተመላክቷል።
የሪፖርቱ ግምገማ በመዋቅራዊ ለውጥ፣ በዘርፍ ትራንስፎርሜሽን እና በጠነከረ ዓለም አቀፋዊ ተሳትፎ ላይ የተመሠረተ ተወዳዳሪ፣ አካታች እና የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት እየተደረገ ያለውን ተጨባጭ መሻሻል አመላክቷል
Apr 20, 2026 200
የሪፖርቱ ግምገማ በመዋቅራዊ ለውጥ፣ በዘርፍ ትራንስፎርሜሽን እና በጠነከረ ዓለም አቀፋዊ ተሳትፎ ላይ የተመሠረተ ተወዳዳሪ፣ አካታች እና የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት እየተደረገ ያለውን ተጨባጭ መሻሻል ማመላከቱን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታወቀ። ጽህፈት ቤቱ የ100 ቀናት ግምገማ እና የ9 ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርትን በተመለከተ ባወጣው መረጃ:- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት በዛሬው ዕለት በቀረበው የ100 ቀናት ግምገማ እና የ9 ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት፣ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ(ዶ/ር) ቁልፍ ማሻሻያዎችንና የተመዘገቡ ስኬቶችን አብራርተዋል። ‎ሪፖርቱ ቀደም ሲል ደካማ ተቋማዊ አቅም፣ ዝቅተኛ ምርታማነት፣ ውስን የግል ዘርፍ ተሳትፎ እና ውጤታማ ያልሆኑ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይስተዋሉበት በነበረው አስቸጋሪ የኢኮኖሚ ሁኔታ ውስጥ የተከናወኑ ተግባራትን ያካተተ ነው። መንግሥት ለእነዚህ ተግዳሮቶች ምላሽ ለመስጠት ኢኮኖሚውን ለውድድር ክፍት ማድረግን፣ ሀገር በቀል ፖሊሲዎችን ማራመድ እና በተለያዩ ዘርፎች እድገትን ማዕከል ያደረገ ተጨባጭ የሪፎርም አጀንዳ ተግባራዊ አድርጓል። ‎ይህም በካፒታል ገበያ ልማት፣ በመንግሥትና በግል እንዲሁም በመንግሥትና በሕዝብ አጋርነት በተዘረጉ አዳዲስ የፋይናንስ ሥርዓቶች የታገዘ ሲሆን፤ በተቀናጀ የክትትል ሥርዓት እና ፈጣን የፕሮጀክት አፈጻጸም አማካኝነት የኢኮኖሚ አስተዳደር እንዲጠናከር ተደርጓል። ‎በዚህ ለውጥ ውስጥ የግሉ ዘርፍ ለኢኮኖሚ ዕድገት ቁልፍ ሞተር እንዲሆን ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ሲሆን፣ ይህም በጠንካራ የልማት አጋርነትና በስራ ላይ ባለው የዕዳ ሽግሽግ (debt restructuring) የተደገፈ ነው። ‎በተመሳሳይ የተቋማዊ ሪፎርም፣ የማኅበራዊ አካታችነት እና የአገልግሎት አሰጣጥ ማሻሻያ ሥራዎች ተደራሽነትን ለማስፋት፣ ጥራትን ለማረጋገጥና የአስተዳደር መዋቅሮችን ለማጠናከር አልመው ተከናውነዋል።   በዓለም አቀፍ ደረጃ ደግሞ ዜጋ ተኮርና ንቁ ዲፕሎማሲ ቀጣናዊ ትስስርን እና የኢትዮጵያን ተሰሚነት አሳድጓል። የብሪክስ (BRICS+) አባልነት፣ በንግድና ኢንቨስትመንት ላይ ያተኮሩ አጋርነቶች መስፋፋት፣ በአየር ንብረት ዲፕሎማሲ የታየው መሪነት እና የኮፕ 32 (COP32) ጉባኤን ለማስተናገድ የተመረጠችበት ስኬት እንዲሁም የባሕር በር ለማግኘት የሚደረገው ጥረት ተጠቃሽ ስኬቶች ናቸው። እነዚህ ማሻሻያዎች ወደ ተጨባጭ የኢኮኖሚ ውጤቶች ተቀይረዋል። ‎በአሁኑ ወቅት የኢኮኖሚ ዕድገቱ 9.2 በመቶ የደረሰ ሲሆን ወደ 10.2 በመቶ እንደሚያድግ ይጠበቃል። ባለፉት ስምንት ዓመታትም በአማካይ 7.5 በመቶ ዕድገት ተመዝግቧል። የኢንቨስትመንት ከባቢው በከፍተኛ ሁኔታ መሻሻሉን ተከትሎ 2,153 የኢንቨስትመንት ፈቃዶች የተሰጡ ሲሆን (65 በመቶው በማምረቻ ዘርፍ ነው)፤ የመንግሥት የልማት ድርጅቶችም ከነበሩበት የ8 ቢሊዮን ብር ኪሳራ ወጥተው ባለፉት ዘጠኝ ወራት 2.1 ትሪሊዮን ብር ገቢ ማስገኘት ችለዋል። በዚሁ የዘጠኝ ወራት ውስጥ ወደ 96,000 የሚጠጉ የሥራ ዕድሎች ተፈጥሯል። ‎የዘርፍ አፈጻጸምን በተመለከተ የግብርና ሜካናይዜሽን ማደግ፣ የማምረቻ ዘርፍ የገበያ ድርሻ ከ25 ወደ 46 በመቶ ከፍ ማለቱ፣ የወርቅ ኤክስፖርት በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩ፣ የቱሪዝም ኢንቨስትመንትና መዳረሻዎች መስፋፋት እንዲሁም በ4ጂ (4G) እና 5ጂ (5G) ኔትወርክ ዝርጋታ፣ በዲጂታል የመንግሥት አገልግሎቶችና በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) ተቋማት አማካኝነት የታየው ፈጣን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን በሪፖርቱ ተመላክቷል። ‎በተጨማሪም በአረንጓዴ ልማትና በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ረገድ በአካባቢ ጥበቃ፣ በልቀቃ ቅነሳ እና የአየር ንብረት ለውጥን በሚቋቋም ግብርና ላይ እድገት ታይቷል። የሰብዓዊ ድጋፍ ሥርዓቱም የአደጋ ስጋት ክምችት አቅምን በማሳደግ፣ የመጋዘን መሠረተ ልማትን በማስፋፋት፣ የቅድመ ማስጠንቀቂያና ድንገተኛ ምላሽ አሰጣጥን በማሻሻል እንዲሁም የሕዝብ ተሳትፎን በመጨመር እንዲጠናከር ተደርጓል። ‎በአጠቃላይ የሪፖርቱ ግምገማ በመዋቅራዊ ለውጥ፣ በዘርፍ ትራንስፎርሜሽን እና በጠነከረ ዓለም አቀፋዊ ተሳትፎ ላይ የተመሠረተ ተወዳዳሪ፣ አካታች እና የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት እየተደረገ ያለውን ተጨባጭ መሻሻል አመላክቷል።
የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ የግሉን ዘርፍ በማጠናከር ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንትን መሳብ ችሏል
Apr 20, 2026 166
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ የውጭ ምንዛሪ በገበያ እንዲወሰን በማድረግና የግል ኢንቨስትመንትን ተሳትፎ በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገቡን የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው ገለጹ። የአውሮፓ ሕብረት እና ኢትዮጵያ የቢዝነስ ፎረም " ዓለም አቀፍ የገበያ መግቢያ አቅምን መጠቀም" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ሰመሪታ ሰዋሰው በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት ዘላቂ ዕድገት ማስመዝገብ የሚያስችል ሁሉን አቀፍ ሪፎርም አድርጋለች። ኢትዮጵያ አካታችና ሁሉን አቀፍ ሪፎርም በማድረግ ያላትን ዕምቅ አቅም መጠቀም የሚያስችል ለውጥ እያመጣች መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያና የአውሮፓ ሕብረት ቢዝነስ ፎረም ኢትዮጵያ ያላትን አቅም ለማውጣት፣ ትብብርን ለመፍጠር፣ የገበያ አማራጮችን ለማሰስ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።   የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ የግሉን ዘርፍ በማጠናከር ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንትን መሳብ መቻሉንም ገልጸዋል፡፡ ከሪፎርሙ በኋላ የውጭ ምንዛሪ ክምችት ጨምሯል፤ የዋጋ ግሽበት ቀንሷል፤ ከወጭ ንግድ የሚገኘው የምንዛሪ መጠን በእጅጉ አድጓልም ብለዋል። ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም በተያዘው ዓመት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በ9 ነጥብ 2 በመቶ እድገት እንደሚያስመዘገብ መተንበዩን በመጥቀስ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ አሕጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናን በመተግበር ምቹ ለኢንቨስትመንት መዳረሻነቷን እያጠናከረች መሆኑን ገልጸዋል። መንግስት የግሉን ዘርፍ ተሳትፎና የዲጂታል ግብይትን ማጠናከር የሚያስችል የዲጂታል ክፍያና አገልግሎት ስርዓት ማዘመኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በብዝሀ የኢንቨስትመንት ዘርፍ ተመራጭ መሆኗን በመጥቀስ፣ የአውሮፓ ሕብረትና አባል ሀገራት ኩባንያዎች በኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ በታዳሽ ሀይል፣ ቴክኖሎጂ፣ ጋርመንትና መሰል ዘርፎች መሰማራት ይችላሉ ብለዋል። ለኢንቨስትመንት ምቹ ሥነ ምህዳርና መሰረተ ልማት በመዘርጋት ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። የአውሮፓ ሕብረትና አባል ሀገራት ወደ ኢትዮጵያ መጥተው መዋዕለ ንዋያቸውን ማፍሰስ እንደሚችሉ ገልጸው፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ለኢንቨስተሮች አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ ነው ብለዋል። የአውሮፓ ሕብረት ዓለም አቀፍ ትብብር ኮሚሽነር ጆዜፍ ሲከላ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት መስራች፣ የቡና መገኛ፣ ለኢንቨስትመንት ምቹ የሆነች ታሪካዊ ሀገር መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ንግድና ኢንቨስትመንትን የሚያጠናክሩ የፖሊሲ እርምጃዎችን በመውሰድ መዳረሻው የት እንደሆነ በግልጽ አሳይታለች ብለዋል። የአውሮፓ ሕብረት ደረጃቸውን የጠበቁ የመሰረተ ልማትና የዲጂታል መሰረተ ልማት ይፈልጋል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ሕብረቱ በገጠር መሰረተ ልማት ግንባታ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። የአውሮፓ ሕብረት እና ኢትዮጵያ ቢዝነስ ፎረም በንግድ ድርጅቶች መካከል፣ በመንግሥት እና በንግድ ድርጅቶች መካከል ገንቢ ውይይት ማድረግ ያስችላል ብለዋል። የአፍሪካ አሕጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ዋና ጸሀፊ ዋምኬሌ ሜኔ፤ በአፍሪካ አሕጉር ከአራት ሺህ ላይ የአውሮፓ ኩባንያዎች በመሳተፍ በዓለም ቀዳሚዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህ ትብብር በአፍሪካ አሕጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸው፤ የተበጣጠሰ የእሴት ሰንሰለት ባለው የዓለም ገበያ በአፍሪካ የበለጠ ተጠቃሚ ይሆናሉ ብለዋል። ኢትዮጵያ የቢዝነስ ስራዎችን የሚያቀላጥፉ የጉምሩክና የፋይናንስ ስርዓቷን እያዘመነች መሆኑን ጠቅሰው፤ የዲጂታል ክፍያ ስርዓት መፈጠሩን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ትርጉም ያለው ሪፎርም በማድረግ ሀገሪቱን በአፍሪካ ባለ ግዙፍ ኢኮኖሚ ባለቤት አድርጓታል ብለዋል። በዚህም ንግድና ኢንቨስትመንት በኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን በላይ የአፍሪካ ሕዝብ መነቃቃት የሚፈጥር የገበያ ሁኔታ መፈጠሩን ገልጸዋል።      
ጥረቶቻችን ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለንን አቋም ያሳያሉ -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 20, 2026 281
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፡- ጥረቶቻችን የበለጠ ጽኑ፣ተወዳዳሪ እና አካታች ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለንን አቋም እና የመተግበር ዐቅም ያሳያሉ ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ የሥራ ዘመኑን ሦስተኛ የ100 ቀናት የመንግሥት ሥራ አፈፃፀም ከዘጠኝ ወራት አጠቃላይ አፈፃፀም ጎን ለጎን መገምገም ጀምረናል ብለዋል።   ‎ለእድገት አመቺ ካልነበረው እና በደካማ የተቋማት እና የፖለቲካ ማዕቀፍ፣ በታጠረ የግል ዘርፍ ተሳትፎ እንዲሁም ውጤታማ ባልነበረ የቁጥጥር ከባቢ ከሚገለጠው የኢኮኖሚ መልክ ወጥተናል ሲሉም ገልጸዋል። የግሉ ዘርፍ ደካማ ውድድር ውስጥ ነበር ሲሉም አውስተዋል። በመንግሥት ሥር የነበሩ በርከት ያለ ቁጥር ያላቸው የንግድ ተቋማትም ከፍ ባለ የዕዳ ሸክም ተዘፍቀው ከዐቅም በታች ሲንቀሳቀሱ እንደነበር ይታወቃል ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ምርታማነት አሽቆልቁሎ ኢኮኖሚውም ለአየር ንብረት ለውጥ በከፍተኛ ደረጃ ተጋላጭ የነበረውን ነባራዊ ሁኔታ ምላሽ በሚሰጥ አዲስ ገቢር ነበብ የፖለቲካ ኢኮኖሚ መንገድ ቀይሰናል ሲሉም አስታውቀዋል።   የቀየስነው አዲሱ የኢኮኖሚ አካሄድ በአጭር ጊዜ ትግበራ ጠንካራ ባለሁለት አሃዝ የእድገት ሂደትን አስመዝግቧል ብለዋል በመልዕክታቸው። በአሁኑ ወቅት ኢኮኖሚያችን በ9 ነጥብ 2 በመቶ እያደገ ይገኛል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)፤ይኽ እድገት በመጪው ዓመት ወደ10 ነጥብ 2 በመቶ እንደሚያድግ እንጠብቃለን ሲሉ አመላክተዋል። በየዘርፉም የታቀዱ ግቦቻችንን ለማሳካት ከፍ ባለ ትጋት ቀጥለን፤ በግብርና 7 ነጥብ 9 በመቶ፣ በኢንዱስትሪ 13 ነጥብ 2 በመቶ፣ በአገልግሎት 9 ነጥብ 3 በመቶ ዕድገቶች ሳይቆራረጡ የሚከናወኑ ይሆናል በማለት ገልጸዋል።   ‎እነዚህ ጥረቶች የበለጠ ጽኑ፣ተወዳዳሪ እና አካታች ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለንን አቋም እና የመተግበር ዐቅም ያሳያሉ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)።
አሜሪካ ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን የምታደርገውን ድጋፍ ለማጠናከር ቁርጠኝነቷን ገለጸች
Apr 20, 2026 312
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ)፦አሜሪካ ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ትራስፎርሜሽን የምታደርገውን ድጋፍ እንደምትቀጥል አስታወቀች። በገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የተመራ ከፍተኛ የልዑካን ቡድን፣በዋሺንግተን ዲሲ ከተካሄደው የዓለም ባንክ እና የአይኤምኤፍ (IMF) የፀደይ ወቅት ስብሰባ ጎን ለጎን፣ከከፍተኛ የአሜሪካ የግምጃ ቤት መሥሪያ ቤት ባለሥልጣናት ጋር በኢኮኖሚያዊ ትብብር ዙሪያ ተወያይቷል። ውይይቱ በዋነኝነት ያተኮረው የንግድ እና የኢንቨስትመንት ግንኙነቶችን በማሳደግ ላይ ሲሆን፣ በተለይም እንደ አዲሱ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ያሉ ስትራቴጂካዊ የኢንቨስትመንት ዕድሎች ላይ ሰፊ ምክክር ተደርጓል። የአሜሪካ ባለሥልጣናት ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለችውን የኢኮኖሚ ሪፎርም አበረታች ሂደት አድንቀዋል። ባለሥልጣናቱ አሜሪካ ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን የምታደርገውን ድጋፍ በቴክኒክ ድጋፍ፣ በግሉ ዘርፍ ተሳትፎ እና ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ጋር በመተባበር እንደምታጠናክርም በድጋሚ አረጋግጠዋል። ሁለቱም ወገኖች ቅድሚያ በሚሰጧቸው የጋራ የኢኮኖሚ ጉዳዮች ወደፊት ለማራመድ፣ ዕድገትን ለማፋጠን እና የሁለቱን አገራት የኢኮኖሚ ትስስር ለማስፋት ስምምነት ላይ መድረሳቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
የምግብ ሉዓላዊነት - ከተረጂነት መላቀቂያው መንገድ
Apr 20, 2026 253
በሙሴ መለሰ ኢትዮጵያ ከተረጂነትና ጠባቂነት መፋቻ መንገዶች መካከል የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ አንዱ ብልኀት አድርጋ እየታተረች ነው። ይህን ተከትሎም የዜጎችን የምግብ ፍላጎት በራስ የምርት ዐቅም የመሸፈን ሥራ በመከወን ከጠባቂነት ለመላቀቅ እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎች ስኬታማ ናቸው። ለዚህም ኢትዮጵያ በስንዴ ልማት ከልመና ወጥታ ወደ ውጭ ገበያ መላክ መጀመሯ አሥረጅ ነው። በመሆኑም ከውጭ የኢኮኖሚ ጥገኝነት በመላቀቅ የዜጎችን የምግብ ሉዓላዊነት ለማስከበር በስንዴ ልማት የተመዘገበውን ስኬት በሌሎች የግብርና ዘርፎች ለመድገም ርብርብ እየተደረገ ነው። በዚህም መሠረት በሩዝ፣ አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ ሻይ ቅጠል እና ሌሎች የተለያዩ ሰብሎች ላይ እየተከናወነ ያለው ሥራ አበረታች ውጤት እያስገኘ ነው። የተባበሩት መንግሥታት የምግብ እና የግብርና ድርጅት (ፋኦ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በምግብ ዋስትናና በተመጣጠነ የምግብ አቅርቦት ላሳዩት ርዕይ፣ የአመራር ቁርጠኝነት የአግሪኮላ ሜዳሊያ በ2016 ዓ.ም ማበርከቱ ለምግብ ሉዓላዊነት ጥረት የተሰጠ ዕውቅና ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ረሃብን ከማስቀረት ባለፈ የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ብሔራዊ ብልጽግናን ዕውን ለማድረግ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በርካታ ያልተነኩ ጥሬ ሃብቶች፣ተስማሚ የዓየር ንብረት፣ ለሥራ ትጉ የሆነ ወጣት እንዳላት እና እነዚህን ሃብቶች ታሳቢ በማድረግ የታሪክ ዐውራ የሆነችውን ሀገር ልማት ወደፊት ለማራመድ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አስረድተዋል። በአንድ ወቅት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስከበር ዋጋ እንደከፈልን ሁሉ፤ ከምግብ ጥገኝነት ለመላቀቅ በትጋት መሥራት ይገባል ሲሉ ማስገንዘባቸው ይታወሳል። የምግብ ሉዓላዊነት፣የቴክኖሎጂ ሉዓላዊነት፣ የበጀት ሉዓላዊነት ታላቁን የሀገር ሉዓላዊነት በጽናት የሚያቆሙ መሆናቸውንም አብራርተዋል። እነዚህን የሉዓላዊነት ዘርፎች ለማስከበርም ብሔራዊ ዐርበኝነት እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል። ሀገራዊ ትልሙ ኢትዮጵያን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለተሟላ ሀገራዊ ክብር፣ ነጻነት እና ሉዓላዊነት የሚያሸጋግር መልካም ጅማሮ ነው። #የምግብ_ሉዓላዊነት #ኢዜአ
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም