ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በጅማ ዞን የተጀመረው የሻይ ቅጠል ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳደገ ነው
Jun 8, 2026 510
ጅማ፣ ሰኔ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በጅማ ዞን የተጀመረው የሻይ ቅጠል ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ይበልጥ የሚያሳድግ መሆኑን የዞኑ አስተዳዳሪ አቶ ቲጃኒ ናስር ተናገሩ። በዞኑ ሸቤ ሶምቦ ወረዳ አርሶ አደሩን ባሳተፈ መልኩ የሻይ ቅጠል ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ዛሬ ተካሂዷል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የዞኑ አስተዳዳሪ አቶ ቲጃኒ ናስር እንደገለጹት፤ ዞኑ ለሻይ ቅጠል ልማት ምቹ በመሆኑ አርሶ አደሩን በክላስተር በማደራጀትና አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሠራ ይገኛል። በዞኑ ከ 60 ሚሊዮን በላይ የሻይ ቅጠል ችግኞች የተዘጋጁ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ከ 20 ሚሊዮን የሚበልጠውን የመትከል ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል።   ባለፉት ሁለት ዓመታት ውስጥ በ 1 ሺህ 600 ሄክታር መሬት ላይ የሻይ ቅጠል ማልማት መቻሉን ጠቅሰው፤ የሻይ ቅጠል ልማቱን ይበልጥ አስፋፍቶ ምርቱን ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የሚያስችል የሻይ ቅጠል ፋብሪካ የማቋቋም ሥራ በትኩረት እየተሠራበት ይገኛልም ነው ያሉት። የሸቤ ሶምቦ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ መሐመድሳኒ አባ ኦሊ በበኩላቸው፤ በወረዳው በአሁኑ ወቅት በ 500 ሄክታር መሬት ላይ የሻይ ቅጠል እየለማ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪም በኩታ ገጠም ተደራጅተው ወደ ሥራው ለገቡ አርሶ አደሮችና ወጣቶች ሰፊ የሥራ ዕድል መፈጠሩንና ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን አክለዋል።   የወረዳው አርሶ አደሮች የሆኑት አባ ዝናብ አባዋይ እና አህመድ ሼከማል በኩታ ገጠም ተደራጅተው በሻይ ቅጠል ልማት ላይ መሰማራታቸውን ገልጸው፤ ከባለሙያዎች የሚደረግላቸው ድጋፍ ከፍተኛ መሆኑንና ወደ ሥራው በመግባታቸው ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ተናግረዋል። ሌላኛው ወጣት አርሶ አደር ሚፍታህ መሐመድ በበኩሉ፤ በአሁኑ ወቅት ከሌሎች ወጣቶች ጋር ተደራጅቶ የሻይ ቅጠል እያለማ መሆኑን ጠቅሶ ወደ ፊት ተጠቃሚ እንደምሆን ትልቅ ተስፋ አለኝ ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል።  
የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ በወተት ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ ነው
Jun 8, 2026 270
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 1/2018(ኢዜአ)፦ የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ በወተት ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አማካሪ ሚኒስትር ደኤታ ኢፋ ሙለታ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት በባዮ ቴክኖሎጂ ምርምር "ኢቲቱ" የተሰኘ ወተት ማርጋት የሚያስችል የፕሮ ባዮቲክ እርሾ ይፋ አድርጓል።   የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የዓለም የወተት ቀንን አስመልክቶ የጋራ የውይይት መድረክ እና አውደ-ርዕይ አካሂዷል። የግብርና ሚኒስቴር አማካሪ ሚኒስትር ደኤታ ኢፋ ሙለታ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ "ኢቲቱ" የፕሮ ባዮቲክ እርሾ ከውጭ የሚገባውን ምርት በማስቀረት የውጭ ምንዛሪን ማዳን የሚያስችል ነው፡፡ ይህም በወተት እና የወተት ተዋጽኦ ምርታማነት ላይ ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመዋል። በተጨማሪም ኢትዮጵያ በግብርና ፖሊሲ የምግብ ዋስትናንና ስነ-ምግብን ለማጠናከር እያከናወነች ያለውን ስራ የሚያግዝ መሆኑን ተናግረዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተተገበረው የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ በወተት ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ባለሀብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረው በዛሬው ዕለት ይፋ የተደረገው "ኢቲቱ" የፕሮ ባዮቲክ እርሾ አምራቹን እና የዘርፉን ተዋንያን የሚያነቃቃ መሆኑን ጠቁመዋል።   የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ንጉሴ ደቻሳ በበኩላቸው "ኢቲቱ" የተሰኘው አዲሱ የፕሮ ባዮቲክ እርሾ በሀገሪቱ ያሉ የወተት ማቀነባበሪያ ድርጅቶች በውጭ ምንዛሪ ከውጭ አስገብተው የሚጠቀሙበትን እርሾ የሚተካ ነው ብለዋል። ይህ የምርምር ውጤት የውጪ ምንዛሪ ወጪን ከማዳን ባለፈ፣ ፓስቸራይዝድ የሆነ ወተትን በአራት ሰዓታት ውስጥ ማርጋት ያስችላል ነው ያሉት። ኢንስቲትዩቱ ምርምር ከሚያደርግባቸው የግብርና ውጤቶች መካከል ወተትና የወተት ተዋጽኦዎች ዋነኞቹ መሆናቸውን ገልጸው፤ ምርቱ ለምግብ ዋስትና እና ለጤንነት ወሳኝ የሆኑ ንጥረ ነገሮችን የያዘ መሆኑን አብራርተዋል። ኢንስቲትዩቱ የተሻሻሉ የሰብል እና የእንስሳት ዝርያዎችን በምርምር በማውጣት ለዘርፉ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል፡፡ በአሁኑ ወቅትም በወተት ምርታማነት ላይ ትኩረት ያደረጉ በባዮ ቴክኖሎጂ የታገዙ ልዩ ልዩ ምርምሮች እየተከናወኑ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። "ኢቲቱ" የፕሮ ባዮቲክ እርሾ ምርታማነትን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያረጋግጥ የገለጹት ደግሞ የሰበታ አግሮ ኢንዱስትሪ ዋና ስራ አስፈጻሚ እና የኢትዮጵያ ዴይሪ ማህበር ፕሬዝደንት ሙልጌታ ይመር ናቸው።   እንዲሁም የምርት ሂደትን የሚያፋጥንና በሀገር ውስጥ መመረቱ ተደራሽነቱንም የሚያረጋግጥ መሆኑን አንስተዋል። የዓለም የወተት ቀን የወተት ምርት ለሥነ-ምግብ እንዲሁም ለኢኮኖሚ ያለው ፋይዳ የሚታሰብበት ሲሆን፣ ዕለቱ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የምግብ እና የግብርና ድርጅት (FAO) አማካኝነት እ.ኤ.አ በ2001 የተቋቋመ ዓለም አቀፍ ሁነት መሆኑ ይታወቃል።
የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የኑሮ ጫናን በመቀነስና ገበያን በማረጋጋት ረገድ ከፍተኛ እፎይታ እየሰጡ ነው
Jun 8, 2026 235
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 1/2018 (ኢዜአ)፦የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የኑሮ ጫናን በመቀነስና ገበያን በማረጋጋት ረገድ ከፍተኛ እፎይታ እየሰጡ መሆኑን አስተያየታቸውን የሰጡ ሸማቾችና ነጋዴዎች ገለጹ። መንግሥት በቅዳሜና እሁድ ገበያዎችና ተግባራዊ ባደረጋቸው የተለያዩ ኢኒሼቲቮች የምርት አቅርቦትን በማሳደግ፣ የዋጋ ንረትን በመቆጣጠር፣ ገበያን በማረጋጋት እንዲሁም የኑሮ ጫናን በማቃለል የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ ይገኛል። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ዋነኛ ዓላማም ሸማቾች ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ማስቻል ሲሆን፤ ገበያዎቹ ምርቶቹን ከአርሶ አደሮች፣ ከፋብሪካዎች ወይም ከሸማቾች የኅብረት ሥራ ማህበራት በቀጥታ በመረከብ እያቀረቡ ይገኛሉ፡፡   ኢዜአ በመዲናዋ በሚገኙ የተለያዩ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ተዘዋውሮ ያነጋገራቸው ሸማቾችና ነጋዴዎች በገበያዎቹ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኙና እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ አስተያየታቸውን ከሰጡት ሸማቾች መካከል አቶ አውላቸው ይልማ እንደገለጹት፤ የሚፈልጉትን ምርት በበቂና በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት ችለዋል። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በአካባቢያቸው መከፈታቸው ለግብይት የሚያስፈልገውን ጊዜና የትራንስፖርት ወጪ እንደቆጠበላቸው ገልጸው፤ የገበያዎቹ በቅርብ ርቀት ተደራሽ መሆን ተጠቃሚዎች በተመጣጣኝ ዋጋ የፈለጉትን ምርት እንዲያገኙ ማስቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ሞልቶታል ጫንያለው በበኩላቸው፤ በመዲናችን አዲስ አበባ በየሳምንቱ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ ዜጎችን የሚያስተናግዱና ለከተማዋ ትልቅ እፎይታን የሚሰጡ የገበያ ስፍራዎች ሆነዋል ብለዋል፡፡ የቅዳሜና እሁድ የገበያ ማዕከላት የከተማዋን ነዋሪ የኑሮ ጫና ለማቅለል እና ገበያ ለማረጋጋት ትልቅ አቅም መሆናቸውንም ጠቅሰው ምርቶችን በቀጥታ ለህዝቡ እንዲቀርቡ በማድረግ የዋጋ ንረትን በማረጋጋት ረገድም ገበያዎቹ ጉልህ ሚና እንዳላቸው ገልጸዋል።   መንግስት ሸማቹንና አምራቹን በቀጥታ ለማገናኘትና የኑሮ ውድነቱን ጫና ለማቃለል የወሰደው ይህ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ማቋቋም እርምጃ፤ በማህበረሰቡ ዘንድ ትልቅ እፎይታንና በጎ ምላሽን ያስገኘ መሆኑን ነጋዴዎችም ጭምር ጠቅሰዋል፡፡ በእሁድ ገበያ ላይ በመሳተፍ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን የሚያቀርቡት እነኚሁ ነጋዴዎች፤ ከኅብረት ሥራ ማህበራት እና ከአቅራቢዎች በቂ ምርት እያመጡ ለኅብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እየሸጡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።   ከነጋዴዎቹ መካከል ዮርዳኖስ መልካሙ እንደገለጹት፤ ገበያው ምርታቸውን በቀጥታ ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማድረስ በእጅጉ እየረዳቸው ይገኛል። ለሸማቹ ማህበረሰብ ከመደበኛው ገበያ ባነሰ ዋጋ ምርቶችን በማቅረብ ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው፣ መንግሥት የገበያ ቦታዎችን በማመቻቸት ምርቶችን ከአቅራቢዎች በቀላሉ በማግኘት ለኅብረተሰቡ ለማቅረብ ማስቻሉን አብራርተዋል።   ሌላኛው ነጋዴ መለሰ ካሳው በበኩሉ፤ ይህም ምርቶችን በበቂ እና በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ ለማቅረብ እጅግ ጥሩ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው አስገንዝቧል። ኅብረተሰቡ በእነዚህ መገበያያ ቦታዎች በመገኘት የሚፈልገውን ምርት በደስታና በእፎይታ እየገዛ መሆኑን የገለጹት ደግሞ ነጋዴው አወቀ ቦልዲስ ናቸው፡፡   የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን በአካባቢያቸው በማገኘታቸው መደሰታቸውን የጠቀሱት አስተያየት ሰጪዎቹ፤ የኅብረተሰቡን ፍላጎት ይበልጥ ለማሟላት የምርት አቅርቦቱን በስፋትና በጥራት ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል፡፡  
በኦሮሚያ ክልል በ240 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ፍራፍሬ እየለማ ነው
Jun 8, 2026 340
አዲስ አበባ፤ሰኔ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በ240 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ፍራፍሬ እየለማ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ክልሉ ለፍራፍሬ ልማት ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በበጀት ዓመቱ 29 ሚሊዮን ኩንታል የፍራፍሬ ምርት መመረቱም ተገልጿል። በኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ የፍራፍሬ ልማት ዳይሬክተር አቶ ቻላቸው አዱኛ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በክልሉ ከለውጡ ዓመታት ወዲህ ለፍራፍሬ ልማት ዘርፍ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ክልሉ ለፍራፍሬ ልማት ምቹ የአየር ንብረት፣ በቂ የዝናብ መጠንና ተስማሚ የአፈር ዓይነት ያለው በመሆኑ ለዘርፉ ምርታማነት ከፍተኛ አቅም ያለው መሆኑን አንስተዋል። በተለይ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የምግብ ስርዓትን ከማሻሻል ረገድ ሚናው የላቀ በመሆኑ በተሰሩት በርካታ ተግባራት ውጤት መመዝገቡን የተናገሩት ዳይሬክተሩ፣ በዚህም የአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት እያደገ ነው ብለዋል። ይህንን ተከትሎ እንደ ፓፓያ፣ ሙዝ፣ ማንጎ፣ ብርቱካን፣ አፕል እና ሎሚ ያሉ ዋና ዋና የፍራፍሬ ዓይነቶች የዞኖቹን መልክዓ ምድርና የአየር ንብረት መሰረት በማድረግ በትኩረት እየለማ ነው ብለዋል። ዘርፉን ውጤታማ ለማድረግ የተሻሻሉ የፍራፍሬ ምርጥ ዘሮችን በመጠቀምና የማስፈጸም አቅምን በማሻሻል ልማቱ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በዚህም በ2013 ዓ.ም ከ90 ሺህ ሄክታር ያልበለጠ የነበረው የፍራፍሬ ልማት፣ በአሁኑ ወቅት ወደ 240 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ እየለማ መሆኑን ተናግረዋል። ክልሉ ለፍራፍሬ ልማት ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በበጀት ዓመቱ 29 ሚሊዮን ኩንታል የፍራፍሬ ምርት መመረቱንም ተናግርዋል። ከዚህ ውስጥም ከ8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሚሆነው የአቮካዶ ምርት መሆኑን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት 2 ሺህ 400 ኩንታል የአቮካዶ ምርት ወደ ውጭ መላኩን አንስተው፣ ዘንድሮም በተሻለ ሁኔታ ለመላክ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። አርሶ አደሮቹ የግብርና ኤክስቴንሽን ፓኬጁን ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እንዲያደርጉ የተለያዩ ሙያዊ ድጋፎችና ስልጠናዎች እየተሰጧቸው መሆኑን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ባለሃብቶች በገበያ ማረጋጋት ሂደት አዎንታዊ ሚና እንዲጫወቱ አግዟል 
Jun 8, 2026 147
ደሴ፤ሰኔ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በተደረገላቸው ድጋፍ ምርታማነታቸውን በማሳደግ በገበያ ማረጋጋት ሂደት ላይ አዎንታዊ ሚና እንዲጫወቱ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ባለሃብቶች ገለጹ። በአማራ ክልል ከ414 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ላስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠቱንም የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታውቋል። በባህር ዳር ከተማ "የአለማየሁ ሀይማኖት ዘይት ፋብሪካ" ሥራ አስኪያጅ አቶ ሀብታሙ እሱባለው ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በኢንቨስትመንት ዘርፍ ለሚነሱ ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ ለማግኘት አግዟል። በንቅናቄው የነበረባቸው ችግር መፈታቱ ምርታማነታቸው እንዲያድግና ገበያ በማረጋጋት ሂደት የድርሻቸውን እንዲወጡ ማስቻሉን ገልጸዋል። ባገኙት ድጋፍ የዘይት ፋብሪካው በአጭር ጊዜ ውስጥ ተገንብቶ ወደማምረት ሥራ መግባቱን የተናገሩት አቶ ሀብታሙ፣ በቀን ከ20 ሺህ ሊትር በላይ ዘይት በማምረት ለህብረተሰቡ እየቀረበ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሌላው በኮምቦልቻ ከተማ የ"ይመር አሊ ዱቄትና ብስኩት ፋብሪካ" ተወካይ አቶ ደረጀ ገብሬ በበኩላቸው፣ መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ በሰጠው ትኩረት የፋብሪካው ምርታማነት እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። "በተለይ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የተደረገልን ድጋፍ ተኪና ለወጪ ንግድ የሚሆኑ ምርቶችን ማምረት እንድንችል አድርጎናል" ያሉት ባለሃብቱ፣ ፋብሪካው ከውጭ ይገባ የነበረን የብስኩት ምርት በሀገር ውስጥ በማምረት መተካቱን ገልጸዋል። የአማራ ክልል ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ተፈሪ ታረቀኝ በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ባለፉት ዓመታት የኢንቨስትመንት ዘርፉ እንዲነቃቃ ማድረጉን ገልጸዋል። ለዚህም በተያዘው በጀት ዓመት ብቻ 414 ቢሊዮን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ 3 ሺህ 518 ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠቱን በማሳያነት አስረድተዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን ገልጸዋል። ችግሮች በቅንጅት እንዲፈቱ፣ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ምርታማነት እንዲጨምር፣ ገበያውን እንዲያረጋጉና ተጠቃሚ እንዲሆኑም ማስቻሉን ተናግረዋል። በቀጣይም የኤሌክትሪክ ኃይል እና የመሬት አቅርቦትን ጨምሮ የዘርፉን ማነቆዎች በመፍታት በኢንዱስትሪው ዘርፍ ከፍተኛ ለውጥ ለማምጣት በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የአማራ ክልል የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ክልላዊ የማጠቃለያ መድረክ ትናንት በኮምቦልቻ ከተማ መካሄዱ የሚታወስ ነው።
የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት መዘመን ለህብረተሰቡ ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት አስችሏል
Jun 7, 2026 947
አዲስ አበባ፤ግንቦት 30/2018 (ኢዜአ)፡-የአዲስ አበባ የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት መዘመን ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘት እንዳስቻላቸው ተጠቃሚዎች ገለጹ፡፡ መንግስት በትራንስፖርት ዘርፉ ላይ እያደረጋቸው ያሉ ሁለንተናዊ ማሻሻያዎችና በመዲናዋ የተገነቡት ዘመናዊ የአውቶብስ ፌርማታዎች ለአገልግሎቱ መቀላጠፍና ለተሳፋሪዎች ምቾት የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው፡፡ በመዲናዋ ደረጃቸውን በጠበቁና ዘመናዊ ተሽከርካሪዎች ለማህበረሰቡ የተሳለጠ የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት ገቢራዊ ተደርጓል፡፡ በአዲስ አበባና በዙሪያዋ በሚገኙ ከተሞች ሳምንቱን ሙሉ ያለማቋረጥ የትራንስፖርት አገልግሎት በማቅረብ ላይ ያሉት የከተማ አውቶብሶች ለነዋሪዎች ኢኮኖሚዊና ማህበራዊ እፎይታን እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ የሆኑት አቶ መኮንን ለገሰ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የብዙሃን ትራንስፖርት ከሌሎች አማራጮች አንጻር አነስተኛ ታሪፍ ያለው በመሆኑ ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ትልቅ አቅም ይፈጥራል፡፡ የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት በተቀመጠላቸው የጊዜ ሰሌዳ የሚንቀሳቀሱ መሆናቸውን ገልጸው፤ ይሄውም ያለ ምንም እንግልት በሰዓታቸው የሥራ ቦታቸው ላይ እንዲገኙ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል፡፡ ገቢያቸውን ያማከለና ተመጣጣኝ የትራንስፖርት አገልግሎት ከማግኘት ባለፈ ለሥራቸው መቃናትና ምርታማነት የጎላ አበርክቶ እንዳለው ጠቅሰዋል፡፡   ሌላኛዋ አስተያየት ሰጭ ወይዘሮ መስከረም ዳመነ፤ አገልግሎቱ በየጊዜው እየተሻሻለ በመምጣቱ ጠዋትም ሆነ ማታ ፈጣን፣ ምቹና ቀልጣፋ ግልጋሎት እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት መዘመን የነዋሪዎች የዕለት ከዕለት እንቅስቃሴ በማሳለጥ ገንቢ አስተዋጽኦ እያደረገ ነው ብለዋል፡፡ የከተማ አውቶብስ አሽከርካሪዎች በበኩላቸው ቴክኖሎጂን መሠረት ያደረገው አዲሱ አሠራር በሥራቸው ላይ ትልቅ መነቃቃት መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡   አቶ ያለው ነጋ በትራንስፖርት ዘርፉ የተተገበረው ሪፎርም በካሜራና ጂፒኤስ (GPS) የታገዘ ዘመናዊ አሰራርን በማምጣት የአሽከርካሪዎችን የቴክኖሎጂ አቅም ማሳደጉን ገልጸዋል፡፡ ቴክኖሎጂው ቀደም ሲል በፌርማታዎች ይስተዋሉ የነበሩትን ሰልፎች በማስቀረት በመዲናዋና ከዙሪያ ከተሞች ለሚመጡ ተጠቃሚዎች ተመራጭ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   ሌላኛዋ አሽከርካሪ ወይዘሮ ፍሬህይወት ኤካ፤ የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎት መዘመን በተለይ ርቀት ላላቸው መስመሮች ከታሪፍ አንፃር እጅግ አዋጭ ነው ብለዋል፡፡  
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የሀገር ውስጥ ፍላጎትን የሚተኩ እና የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኙ ምርቶች በስፋትና በጥራት እንዲመረቱ አስችሏል
Jun 7, 2026 986
ኮምቦልቻ ፤ግንቦት 30/2018 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የሀገር ውስጥ ምርትን በመተካትና ለውጭ ምንዛሬ ግኝት የሚሆኑ ምርቶችን በጥራትና በስፋት በማምረት ረገድ ለዘርፉ እድገት ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለፁ። «ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት» በሚል መሪ ቃል የሚካሄደው የአማራ ክልል ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ክልላዊ የማጠቃለያ መርሐ ግብር በኮምቦልቻ ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል።   የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል እንደገለጹት፤ ንቅናቄው ባለፉት ዓመታት የኢንዱስትሪውን ዘርፍ ለማሳደግና የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት ከፍተኛ ሚና አበርክቷል። ሚኒስትሩ አክለውም፣ በንቅናቄው አማካኝነት ኢንዱስትሪዎችን መደገፍ፣ መሠረተ ልማቶችን ማሟላት፣ የአገልግሎት አሰጣጥን ማዘመንና በተግዳሮቶች ላይ መፍትሔ መስጠት መቻሉን ገልጸው፤ በእነዚህም ዘርፎች ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን አስረድተዋል። በተጨማሪም ንቅናቄው የገቢ ምርቶችን ከመተካትና የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኙ ምርቶችን በጥራትና በብዛት ከማምረት ባሻገር፣ ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል መፍጠር ማስቻሉን ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በአማራ ክልልም ንቅናቄው በርካታ ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩና አዳዲስ ባለሃብቶችም በኢንቨስትመንት ዘርፉ እንዲሰማሩ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል።   የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፤ በክልሉ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ አማካኝነት በኢንዱስትሪና በኢንቨስትመንት ዘርፎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተቻለ ሲሆን፣ ይህም የክልሉን ኢኮኖሚ ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። ንቅናቄው የገቢ ምርቶችን በመተካትና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በማምረት ረገድ ካስገኘው ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ባሻገር፣ ማኅበረሰቡ በሀገር ውስጥ ምርት የመጠቀምና በራሱ ምርት የመኩራት ባሕል እንዲያዳብር ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ተናግረዋል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በቀጣይም ዘርፉን የመደገፍ፣ የማዘመንና የማስፋት ሥራዎችን በማጠናከር ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን ሁሉም ባለድርሻ አካላት የድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። አክለውም የክልሉ መንግሥት ለዚህ ስኬት አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ እንድሪስ አብዱ በበኩላቸው፤ በንቅናቄው አማካኝነት ባለፉት አራት ዓመታት 496 የሚሆኑ አዳዲስና ነባር ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት ሥራ እንዲሸጋገሩ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል።   ከዚህ በተጨማሪም በኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ዘርፉ ከ125 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር መቻሉን ተናግረዋል። አቶ እንድሪስ አክለውም፤ በንቅናቄው አማካኝነት ከባለሀብቶች ጋር በቅርብ በመሥራት ምርቶቻቸውን እንዲያስተዋውቁ፣ የብድር አቅርቦት እንዲያገኙ፣ መሠረተ ልማቶች እንዲሟሉላቸው እንዲሁም ቀጣይነት ያለው የተጠናከረ ድጋፍ እንዲያገኙ መቻሉን ገልጸዋል። በመርሐግብሩ የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና የከተማ አመራሮች፣ ባለሃብቶችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።  
በክልሉ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በበጀት ዓመቱ 158 መካከለኛና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ወደማምረት ገብተዋል-ቢሮው
Jun 7, 2026 515
ኮምቦልቻ፤ግንቦት 30/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በበጀት ዓመቱ 158 መካከለኛ እና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች በአዲስ መልክ ማምረት መጀመራቸው ተገለጸ። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ መላኩ አለበል እንዲሁም ሌሎች የፌዴራልና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ክልላዊ የማጠቃለያ መርሃግብር በኮምቦልቻ ከተማ እየተካሄደ ነው።   የአማራ ክልል ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ተፈሪ ታረቀኝ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ የነበሩ ችግሮችን እየፈታ መጥቷል። በተለይም ባለሃብቱ ያነሳቸው የነበሩ የማስፋፊያና የአዳዲስ ኢንቨስትመንት ቦታዎች ጥያቄን፣ የብድርና የመሰረተ ልማት ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ ለመፍታት ማስቻሉን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ይህም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ከማስፋፋት ባሻገር የማምረት አቅማቸውን በማሳደግ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማስፋት እያገዘ መሆኑን ነው ያስረዱት። በተያዘው በጀት ዓመት ባለፉት ወራት ብቻ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄው 158 መካከለኛና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች በአዲስ መልክ ማምረት መጀመራቸውንም ተናግረዋል። የፌደራልና የክልሉ አመራሮቹ የተለያዩ የኢንዱስትሪ ምርቶችን ተዘዋውረው የተመለከቱ ሲሆን በቀጣይም ከባለሀብቶች ጋር ውይይት ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ ባለው በዚህ መርሃግብር ላይ 145 ኢንዱስትሪዎች ምርትና አገልግሎታቸውን እያስተዋወቁ ይገኛሉ።
የአረንጓዴ ዐሻራ እና የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብሮች ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል
Jun 7, 2026 551
ጋምቤላ፤ ግንቦት 30/2018 (ኢዜአ)፡- የአረንጓዴ ዐሻራ እና የሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብሮች የፈጠሩትን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ስኬታማ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የጋምቤላ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ።   በክልሉ የተተገበሩት የአረንጓዴ አሻራ እና የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብሮች ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ስኬታማነት ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል ጋምቤላ፤ግንቦት 30/2018 (ኢዜአ)፦በጋምቤላ ክልል የአረንጓዴ አሻራ እና የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብሮች የፈጠሩትን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ረገድ ስኬታማ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል፣ የተሸረሸሩ መሬቶችን ለማገገም እና የደን ሽፋንን ለማሳደግ ታስቦ እየተካሄደ ያለ መጠነ-ሰፊ ንቅናቄ ነው። በሌላ በኩል፣ የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር የሀገሪቱን የምግብና ሥነ-ምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የእንስሳት፣ የዶሮ፣ የንብ፣ እንዲሁም የአትክልትና ፍራፍሬ ምርታማነትን በየቤተሰቡ ደረጃ ለማሳደግ ያለመ ነው። እነዚህ ሁለቱ መርሃ-ግብሮች እርስ በርሳቸው የሚደጋገፉ በመሆናቸው፣ በአንድ በኩል አካባቢን ሲጠብቁ በሌላ በኩል ደግሞ ለተቀናጀ የግብርና ልማት መሳካት ትልቅ መሠረት ጥለዋል። በጋምቤላ ክልልም በሁለቱ መርሃግብሮች የተከናወኑት ተግባራት ውጤት እያስገኙ ነው። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንድሮው ቱት ለኢዜአ እንደገለጹት የአረንጓዴ አሸራና የሌማት ትሩፋት መርሃግብሮች የፈጠሯቸውን ምቹ አጋጣሚ በመጠቀም በክልሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ስኬታማ ስራዎች እየተከናወኑ ነው። ቀደም ሲል ለፍጆታ ብቻ ይመረት የነበረው አትክልት አሁን ላይ ሙዝ፣ አቮካዶ፣ ሐባብና ብርቱካንን ጨምሮ ሌሎች አትክልትና ፍራፍሬዎች በአርሶ አደሮችና በባለሃብቶች በስፋት እየተመረቱ ለገበያ እየቀረቡ ነው ብለዋል። በተለይም በማጃንግ ዞን በጎደሬና በመንጌሽ ወረዳዎች አቮካዶና ሙዝን ጨምሮ ሌሎች የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶች ወደ አዲስ አበባና ሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች ለገበያ በስፋት እየቀረቡ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በክልሉ በዘንድሮው ክረምትም ከአረንጓዴ አሻራ ልማቱ ጋር በማቀናጀት አቮካዶን ጨምሮ ከ8 ሚሊዮን በላይ የፍራፍሬና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለቸው ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ኃላፊው ተናግረዋል። በቢሮው የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም አስተባበሪ አቶ ሀብታሙ ገዳሙ እንዳሉት የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ መረሃ ግብር እንደ ሀገር የግብርናውን ዘርፍ ለማገዝ ከተቀረጹት ፕሮግራሞች መካከል አንዱ ነው። በፕሮግራሙ እየተሰሩ ከሚገኙት የእሴት ሰንሰለት ሰብሎች መካከል አቮካዶ፣ ስንዴ፣ በቆሎና ሌሎችም እንደሚገኙበት አስተባበሪው ገልጸዋል። በዘርፉ ልማት ከተሰማሩት አርሶ አደሮች መካከል የጎደሬ ወረዳ ጌለሻ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ሉቃስ ጎርሾ በሰጡት አትያየት አካባቢው አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ ለሁሉም የግብርና ልማት አመች ነው። እናም ሙዝ፣ አቮካዶና ሌሎችንም የሰብል እንዲሁም የአትክልትና ፍራፍሬዎችን በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁመው በገበያ ትስስር በኩልም የመንግስት እገዛ እንሚሹ ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት በሙዝ ልማት በስፋት በመሰማራት ተጠቃሚ መሆኑን የገለጸው ደግሞ የዚሁ ቀበሌ ነዋር ወጣት ሮቤል ሮኬት ነው። በአሁኑ ወቅት ሰባት ሄክታር የሚደርስ ሙዝ በማልማት ምርቱን ወደ አዲስ አበባና ሌሎች አካባቢዎች በመሸጥ ተጠቃሚ መሆኑን ጠቁመው የገበያ ትስስሩ ሊጠናከር ይገበል ብሏል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን በመኽር እርሻ 718 ሺህ ሄክታር መሬት ይለማል
Jun 6, 2026 873
ነቀምቴ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ወለጋ ዞን በመኽር እርሻ 718 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ የሰብል አይነቶች እንደሚለማ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ደረጄ ነገሰ እንደገለጹት፤ በመኽር እርሻ 718 ሺህ ሄክታር መሬት በማልማት ከ24 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል። ለዚህም ለአርሶ አደሩ አስፈላጊ የግብርና ግብዓቶችን በማቅረብ፣ ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። አሁን ላይ ያለው የዝናብ ሁኔታ ለግብርና ሥራው እጅግ አመቺ በመሆኑ፣ አርሶ አደሩ የተሻለ ምርት ለማግኘት በንቃት እየተንቀሳቀሰ መሆኑንም ኃላፊው ጠቅሰዋል። በመኽር እርሻው ከታቀደው መሬት ውስጥ እስካሁን 272 ሺህ 402 ሄክታሩ በዘር መሸፈኑን አቶ ደረጄ ገልጸዋል። ከግብዓት አንጻርም 473 ሺህ 379 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ ቀርቧል ብለዋል። ዞኑ በበቆሎ ምርት የሚታወቅ በመሆኑ ልዩ ትኩረት የተሰጠው ሲሆን፣ እስካሁን 255 ሺህ 92 ኩንታል የምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ተደርጓል ነው ያሉት። የምስራቅ ወለጋ ዞን የጉቶ ጊዳ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አለማየሁ ሙላቱ በበኩላቸው፤ በወረዳው 64 ሺህ 139 ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ እስካሁን 30 ሺህ 568 ሄክታሩ መልማቱን ተናግረዋል። በወረዳው ዘንድሮ ግብዓት በወቅቱ በመቅረቡ ምንም ዓይነት የእጥረት ስጋት እንደሌለ የጠቆሙት ኃላፊው፤ እስካሁን 47 ሺህ 166 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ እና 5 ሺህ 124 ኩንታል ምርጥ ዘር መሰራጨቱን አስረድተዋል። የጉቶ ጊዳ ወረዳ አርሶ አደር አብዲሳ ቀናቴ፤ ማሳቸውን በክላስተር በማረስ በበቆሎ ዘር ለመሸፈን እየሰሩ መሆኑን ገልጸው፤ ዘንድሮ የተሻለ ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውን ተናግረዋል። ሌላኛው አርሶ አደር አቶ ተስፋ ይማም በበኩላቸው፤ በመኽር ወቅቱ 14 ሄክታር መሬት በበቆሎ ሰብል ለመሸፈን እያረሱ እንደሚገኙ ጠቅሰው፤ ያገኘነውን የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በአግባቡ በመጠቀም የተሻለ ምርት ለማግኘት እየተጋሁ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ ቀጣናዊ የኃይል ትስስርን ለማጠናከር በትኩረት መስራቷን ትቀጥላለች
Jun 6, 2026 721
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ቀጣናዊ የኃይል ትስስርን ለማሳደግ የምታከናውናቸውን ተግባራት አጠናክራ እንደምትቀጥል የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ ገለፁ። የኢትዮጵያን ልማትና ብልፅግና ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ግንባታዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ ለኢዜአ እንዳሉት ኢትዮጵያ ለታዳሽ ኃይል ልማት በትኩረት እየሰራች ትገኛለች። ባለፉት ዓመታት የታላቁ ህዳሴ ግድብን ጨምሮ ሶስት ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ወደስራ ማስገባት መቻሉን ገልፀዋል። ኢትዮጵያ በታዳሽ ኃይል ልማት በስፋት መስራቷ በዘርፉ ተጠቃሽ ከሆኑ ሀገራት መካከል አንዷ እንድትሆን ያስቻላት መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የምታመነጨው የኤሌክትሪክ ኃይል ሙሉ በሙሉ ከታዳሽና ንፁህ ኃይል የሚገኝ መሆኑንም አስረድተዋል። ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ የኃይል ትስስር ተቋም ውስጥ በግንባር ቀደምነት እየሰራች መሆኗን አንስተው፤ ቀጣናዊ የኃይል ትስስርን ለማጎልበት የምታከናውነውን ተግባር አጠናክራ መቀጠሏንም ገልፀዋል። ኢትዮጵያ ኃይል ከምታቀርብላቸው ከጅቡቲ፣ ሱዳንና ኬንያ በተጨማሪ ወደ ታንዛኒያ የኃይል ሽያጭ ሙከራ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው ከሌሎች ሀገራት ጋርም በኃይል ለመተሳሰር ጥናት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ለውጭ ሀገራት የምታቀርበው ከምታመነጨው ኃይል አስር በመቶ ያነሰ እንደሆነ በመግለጽ፤ የሀገር ውስጥና ለውጭ ሀገራት የምታቀርበውን ኃይል በማቀናጀት በታዳሽ ኃይል ቀዳሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። ግዙፍ ኃይል የማመንጨት አቅም ያለው የኮይሻ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ግንባታ እየተከናወነ መሆኑንና በፍጥነት ለማጠናቀቅ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። 16 የኃይል ማስተላለፊያና ማከፋፈያ ጣቢያዎች ፕሮጀክቶችም በግንባታ ሂደት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው፤ ተቋሙ የኢትዮጵያን ልማትና ብልፅግና ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በክልሉ ሳምንቱን ሙሉ ምርት የሚያቀርቡ የግብይት ማዕከላትን በማቋቋም ለማህበረሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ ምርት እየቀረበ ነው 
Jun 6, 2026 472
ሆሳዕና፤ ግንቦት 29/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ ለማቅረብ በተቋቋሙ የግብይት ማእከላት ከእሁድ እስከ እሁድ ምርቶች እየቀረቡ እንደሚገኝ የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ገለፀ። የቢሮው ምክትልና የግብይት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ደስታ ዶሌቦ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክልሉ አምራቹንና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ምርቶችን በግብይት ማዕከላት በስፋት የማቅረብ ስራ ትኩረት ተሰጥቶታል። በዚህም በክልሉ ከ140 በላይ ከእሁድ እስከ እሁድ ምርት የሚቀርብባቸው የግብይት ማዕከላትን በማቋቋም ለማህበረሰቡ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል።     ቢሮው በክልሉ 5 ከተሞች ዘመናዊ የግብይት ማዕከላት ማስገንባቱንና የወራቤ ከተማ ዘመናዊ የግብይት ማዕከል ለአገልግሎት ክፍት መደረጉን አስታውሰዋል። የግብይት ማዕከሉ አምራችና ሸማቹን ማህበረሰብ በቀጥታ በማገናኘት ምርትን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ ማስቻሉን ገልጸዋል። የስልጤ ዞን ነጋዴ ሴቶች ማህበር ፕሬዚዳንት ሽታ መሀመድ በበኩላቸው፤ ከዚህ ቀደም የሚያመርቱትን ምርት በቀላሉ ለማህበረሰቡ ለማቅረብ የሚያስችል የግብይት ማዕከል ባለመኖሩ ገበያ ወዳለበት ስፍራ ይጓዙ እንደነበር ተናግረዋል።     በወራቤ ከተማ ተገንብቶ የተጠናቀቀው ዘመናዊ የግብይት ማዕከል የሚያመርቱትን ምርት ለማህበረሰቡ በቀላሉ ለማቅረብ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። በከተማው ስራ የጀመረው የግብይት ማዕከል የሚፈልጉትን ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ በመግዛት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ያስቻለ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የወራቤ ከተማ ነዋሪዋ ወይዘሮ ሳድያ ጀማል ናቸው።     በከተማው ግንባታው ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቃው ዘመናዊ የግብይት ማዕከል ምርትን በጥራትና በፈለጉት ጊዜ ለማግኘት ማስቻሉን ተናግረዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በቅርቡ በወራቤ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትንና ዘመናዊ የግብይት ማዕከልን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ማድረጋቸው ይታወሳል።
በዞኑ አርሶ አደሮች የቆላ ፍራፍሬን በኩታ ገጠም በማልማት ተጠቃሚ እየሆኑ ነው
Jun 6, 2026 310
ገንዳ ውሃ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን የቆላ ፍራፍሬን በኩታ ገጠም በማልማት የአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት እያደገ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የመስኖና ውኃ አጠቃቀም ባለሙያ አቶ አስናቀው አራጋው እንደገለጹት፤ በዞኑ ለአካባቢው ሥነ-ምሕዳርና የአየር ንብረት ተስማሚ የሆኑ የሙዝ፣ የማንጎ፣ የፓፓያና የዘይቱን ፍራፍሬዎች በኩታ ገጠም ዘዴ እየለሙ ይገኛሉ። ይህንን ተግባር ይበልጥ በማስቀጠልም በመጪው ክረምት 200 ሄክታር መሬት በመተማና በምዕራብ አርማጭሆ ወረዳዎች በኩታ ገጠም ለማልማት የጉድጓድ ቁፋሮ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ለተከላው የሚያስፈልጉ የቆላ ፍራፍሬ ችግኞችም በበጋው ወራት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። የፍራፍሬ ልማቱን ውጤታማ ለማድረግ የባለሙያ ድጋፍና የተሻሻሉ ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ በማቅረብ፣ የሕዝቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሠራ እንደሚገኝም አቶ አስናቀው አስገንዝበዋል። ቀደም ሲል የተተከሉ የፍራፍሬ ምርቶች የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ከመደገፍ ባለፈ፣ ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ሀብት ማፍራት ማስቻላቸውንም ገልጸዋል። በዞኑ መተማ ወረዳ ወዲ ገምዞ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ሲሳይ ይመር በበኩላቸው፤ ለአካባቢው ሥነ-ምሕዳር ተስማሚ የሆኑ የቆላ ፍራፍሬዎችን በማልማት ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን ገልጸዋል። ካለፉት ዓመታት ያገኙትን ልምድ በመጠቀምም በመጪው ክረምት ልማቱን ከአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር ጋር በማስተሳሰር፣ የቆላ ፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል የጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ሌላው የዞኑ የምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ታርቆ አያሌው በበኩላቸው፤ ፍራፍሬን በተበታተነ ማሳ ከመትከል ይልቅ በኩታ ገጠም ማልማት ግብዓትን፣ ቴክኖሎጂንና ጉልበትን በጋራ በመጠቀም ምርታማ ለመሆን ያግዛል ብለዋል። ከዚህ በፊትም በሙዝ ልማት የተሳተፉ መሆናቸውን የገለጹት አርሶ አደሩ፣ አሁን ደግሞ በስፋት በማልማት የገቢ ምንጫቸውን ለማሳደግ እየሠሩ እንደሚገኙ አስገንዝበዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን ባለፉት ዓመታት ከ1 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት በቆላ ፍራፍሬ የለማ መሆኑን ከዞኑ ግብርና መምሪያ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው ዓመት 370 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ ይተከላል
Jun 6, 2026 244
ጅማ ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው ዓመት 370 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ እንደሚተከል የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በጅማ ዞን ማና ወረዳም የዘንድሮው የቡና ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በይፋ ተጀምሯል። በስፍራው ተገኝተው መርሃ ግብሩን ያስጀመሩት የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ ፤ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ በማቅረብ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተሰራው ስራ ውጤት እያመጣ መሆኑን ገልጸዋል።   ዘንድሮ 2 ነጥብ 8 ቢሊዮን የቡና ችግኞች ተዘጋጅተው በ370 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ እየተተከሉ መሆኑን እና ይህም የክልሉን አጠቃላይ የቡና ምርት ሽፋን ወደ 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሄክታር ከፍ እንደሚያደርገው ገልጸዋል። በቀጣይም ምርታማነቱን ይበልጥ ለማሳደግ ከግብርና ምርምር ማዕከላት ጋር በመተባበር የተሻሻሉ ዝርያዎችን የማቅረቡ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የጅማ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ቲጃኒ ናስር በበኩላቸው፤ ባለፉት ዓመታት 300 ሺህ ሄክታር ብቻ የነበረው የዞኑ የቡና ሽፋን አሁን ላይ ከ600 ሺህ ሄክታር በላይ መድረሱን ተናግረዋል።   በዘንድሮው ዓመትም 700 ሚሊዮን ችግኞችን ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ለመትከል ታቅዶ ስራው ተጀምሯል ብለዋል። የማና ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሰመሩዲን አህመድ፤ በወረዳው 9 ሺህ ሄክታር መሬት በቡና ለመሸፈን ታቅዶ በተጀመረው ስራ፣ በዛሬው ዕለት ብቻ በህዝብ ተሳትፎ በ100 ሄክታር መሬት ላይ ችግኝ መተከሉን ገልጸዋል።   የወረዳው አርሶ አደሮች በክላስተር ተደራጅተው በመስኖ ማልማት ከጀመሩ ወዲህ ምርታማነታቸው በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንም አክለዋል። የማና ወረዳ ዶዩ ቢቂላ ቀበሌ አርሶ አደሮች የሆኑት ጋሊ አባዝናብ እና ሀፊዝ በድሩ በሰጡት አስተያየት፤ ከዚህ ቀደም ቡናን በግላቸው ለማምረት ባደረጉት ጥረት ያገኙት የነበረው ምርት አነስተኛ እንደነበር አስታውሰዋል።   "አሁን ላይ ግን በክላስተር ተደራጅተን ማምረት በመጀመራችን ተጠቃሚ መሆን ችለናል፤ ምርትና ምርታማነታችንም እያደገ መጥቷል" ብለዋል። አርሶ አደሮቹ አክለውም፣ በአሁኑ ወቅት አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገላቸው በመሆኑ በዘንድሮው የምርት ዘመን ከፍተኛ ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል።
አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች የአርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት በተጨባጭ እየቀነሱ ነው
Jun 6, 2026 127
መቱ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የተገነቡ አነስተኛና መለስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች፣ በአርብቶ አደር አካባቢዎች የሚያጋጥመውን የውሃ እጥረትና ድርቅ ለመቋቋም የሚያስችል አቅም እየፈጠሩ መሆኑን የክልሉ የመስኖና አርብቶ አደሮች ልማት ቢሮ ገለጸ። የቢሮው ኃላፊ ኢንጂነር ግርማ ረጋሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በውሃ እጥረት ምክንያት በሰዎችና በእንስሳት ላይ የሚደርሰውን የድርቅ ጉዳት ለመቋቋም 'ፊና' የተሰኘ ፕሮጀክት እየተተገበረ ይገኛል። በፕሮጀክቱ አማካኝነት 73 አነስተኛ እና መለስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው ከእነዚህም ውስጥ የ40ዎቹ ግንባታ ተጠናቆ ለአገልግሎት በቅተዋል ብለዋል። በአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ ዘንድ እየተተገበሩ ያሉት እነዚህ የ“ፊና” ፕሮጀክቶች፣ የድርቅ አደጋን የመቋቋም አቅምን በመገንባት ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከቱ መሆኑን ኃላፊው ጠቁመዋል። በተለይም በቦረና፣ በሐረርጌና በባሌ ዞኖች በአርብቶ አደር አካባቢዎች በድርቅ ምክንያት በሰዎችና በእንስሳት ላይ ይከሰት የነበረውን ችግር ለመቅረፍ ፕሮጀክቶቹ ከፍተኛ እገዛ ማድረጋቸውን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ፕሮጀክቶቹ የአካባቢውን ማህበረሰብ ከድርቅ ተጋላጭነት በከፍተኛ ሁኔታ እየታደጉ መሆኑንም አንስተው በቀጣይም ልምዱን ሌሎች የውሃ እጥረት ወደሚያጋጥማቸው አካባቢዎች በማስፋፋት፣ ሊከሰት የሚችለውን ችግር አስቀድሞ ለመከላከልና ለመቋቋም በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። እነዚህ የመስኖ ፕሮጀክቶች ሙሉ በሙሉ ተጠናቅቀው ወደ አገልግሎት ሲገቡ የአካባቢውን የውሃ እጥረት በዘላቂነት ከመቅረፍ ባለፈ በአርብቶ አደሩ ዘንድ በከብት እርባታ ላይ ብቻ የተደገፈውን ህይወት፣ ከግብርና ልማት ስራዎች ጋር በማስተሳሰር ይበልጥ ተጠቃሚ እንደሚያደርጉም ገልጸዋል ።
በክልሉ ዘመናዊ የግብር አሰባሰብን ተግባራዊ በማድረግ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመፍታት ትኩረት ተደርጓል
Jun 6, 2026 122
ባህር ዳር ፤ ግንቦት 29/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ዘመናዊ የግብር አሰባሰብን ተግባራዊ በማድረግ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ ለመፍታት ትኩረት መደረጉ ተገለፀ። በክልሉ ውስጥ የገቢ አቅምን በማሳደግ የህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ ለመፍታት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛል። የገቢ የመሰብሰብ አቅሙን ለማሳደግም የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችን ተግባራዊ በማድረግ ውጤታማ ስራዎችን ማከናወን እንደተቻለ ተመላክቷል። በክልሉ ገቢዎች ቢሮ የግብር ትምህርትና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ታዘባቸው ጣሴ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ የመሰብሰብ ስራ በትኩረት እየተከናወነ ነው። ለዚህም ይረዳ ዘንድ የህግ ተገዥነትን በማሳደግና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም በዚህ በጀት ዓመት ከ100 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ እየተሰራ ይገኛል። እስከ ግንቦት 20/2018 ዓ.ም ድረስ በተቀናጀ መንገድ በተሰበሰበ ገቢም የዕቅዱን ከ73 በመቶ በላይ ማከናወን እንደተቻለ አመልክተዋል። የተሰበሰበው ገቢም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር የ28 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው አስረድተዋል። ተጨማሪ ገቢው የተገኘው ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከርና በቴክኖሎጂ የታገዘ ክትትልና ቁጥጥር በመደረጉ መሆኑን አንስተዋል። እንዲሁም ከዚህ ቀደም በግብር ስርዓቱ ውስጥ ያልነበሩ ግብር ከፋዮችን ወደ ግብር ስርዓቱ ማስገባት በመቻሉ መሆኑንም አክለዋል። በሌላ በኩል በ259 የታክስ ማዕከላት የተቀናጀ የመንግስት የግብር አስተዳደር ስርዓት ተደራሽነትን በማሳደግ የተሟላ አገልግሎት ማቅረብ እንደተቻለ አመልክተዋል። በግብር አሰባሰብ ሂደቱ ቅሬታ ላቀረቡ 46 ሺህ 285 ግብር ከፋዮች ያቀረቡትን ቅሬታ በመመርመር አፋጣኝ ውሳኔ መስጠት መቻሉንም ገልፀዋል። በተቋሙ ውስጥ የስነ ምግባር መጓደል የተስተዋለባቸው ባለሙያዎች ላይ ከስራ እስከ ማሰናበት የሚያደርስ ቅጣት መወሰኑን አብራርተዋል። በቀጣይም የግብር አሰባሰብ አሰራሩን በማዘመን ዕቅዱን ሙሉ በሙሉ ለማሳካት ርብርብ ይደረጋል ነው ያሉት።
የሕዳሴ ግድብ ለቀጣናው ሀገራት የኃይል አቅርቦትን ከማረጋገጥ ባለፈ በትብብር ላይ የተመሠረተ ግንኙነትን ለማጠናከር ያግዛል
Jun 5, 2026 682
አሶሳ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለቀጣናው ሀገራት የኃይል አቅርቦትን ከማረጋገጥ ባለፈ በትብብር ላይ የተመሠረተ ግንኙነትን ለማጠናከር እንደሚያግዝ ተመላከተ። የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ቀጣናዊ ትብብርን በማሳለጥ እና የአባይ ተፋሰስን በዘላቂነት ማልማት ላይ ያተኮረ 4ኛው አለም አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስ አካሂዷል።   በወቅቱም በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ዘሪሁን አበበ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሁፍ እንደገለፁት፤ ሕዳሴ ግድብ ለቀጣናው ሀገራት የኃይል አቅርቦትን ከማረጋገጥ ባለፈ በትብብር ላይ የተመሠረተ ግንኙነትን ለማጠናከር ያግዛል። ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ያላትን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተከናወኑ የሚገኙ የምርምር ስራዎችን በማጠናከር ሀሰተኛ ክሶችንና መረጃዎችን መመከትና እውነቱን ማስረዳት ከምሁራን ይጠበቃል ብለዋል። የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ለግድቡ ቅርብ ከመሆኑ የተነሳ መሰል የጥናትና ምርምር ስራዎችን በማጠናከር የሕዳሴ ግድብ ከኢትዮጵያ ባለፈ ለቀጣናው ሀገራት የሚያስገኘውን ፋይዳ ማሳወቅ እንደሚገባው አመልክተዋል።   የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ያሬድ ሙሉ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በግድቡ አካባቢው የሚኖረው ማህበረሰብ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በኮንፈረንሱ ላይ የአፍሪካና የአውሮፓ ሀገራት የዘርፉ ተመራማሪዎች በበይነ መረብ ጥናታቸውን ያቀረቡ ሲሆን በግድቡ እና በአባይ ተፋሰስ ልማት ዙሪያ ዓለም አቀፍ ተሞክሮዎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
በክልሉ የግብርና ቴክኖሎጂን በስፋት በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 5, 2026 413
መቱ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል የእርሻ መሬትን ከማስፋፋት ባለፈ የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማጎልበት ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ። በኢሉአባቦር ዞን የመኸር አዝመራ በተጠናከረ መልኩ የቀጠለ ሲሆን በዛሬው ዕለት በዶረኒ ወረዳ የተዘጋጀ መሬት በበቆሎ ዘር የመሸፈን ስራ ተጀምሯል።   በዚሁ ጊዜ የኦሮሚያ ክልል መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ግርማ ረጋሳ፤ በክልሉ የበጋና ክረምት እርሻ ስራ በስፋት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በተለይም በክልሉ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በመስኖ ልማት ስራ ትልቅ ውጤት መገኘቱን ጠቅሰው የአነስተኛ እና መለስተኛ መስኖ ልማት ግድቦች ግንባታ መጠናከሩንም ገልጸዋል። የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚቻለው በዋናነት ግብርናን በማስፋፋት መሆኑን የገለጹት ኢንጂነር ግርማ፣ በበጋ ስንዴ ልማት በክልሉ ትልቅ ስኬት መመዝገቡን አስታውሰዋል። ይህም ቀድሞ የነበረውን በዓመት አንዴ የማምረት ባህል በማሻሻል፣ ለክረምት እርሻው ተጨማሪ ትልቅ አቅም መፍጠሩን ገልጸዋል። በተያዘው የመኸር አዝመራም ለግብርና ልማት መዋል የሚችለውን መሬት አሟጦ በማረስ እና የግብርና ሜካናይዜሽንን በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል ብለዋል።   በኢሉአባቦር ዞን በክረምት እርሻ 389 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ለመሸፈን እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ ናቸው። በዞኑ ወረዳዎች የኩታ ገጠም እርሻዎችን በዘር የመሸፈን ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉንም አንስተዋል። በሁሉም ወረዳዎች ምርታማነትን የሚያሳድግ የግብርና ሜካናይዜሽን አቅርቦት እያደገ መምጣቱን የጠቀሱት ዋና አስተዳዳሪው፣ የክረምት እርሻው በትራክተር በመታገዝ እንዲታረስ ትኩረት መሰጠቱን አክለዋል።   የዶረኒ ወረዳ ግብርና ልማትና መሬት አስተዳደር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ለሊሴ አመና በበኩላቸው፣ በወረዳው በክረምት እርሻ ከ17 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች የማልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህም በተለይ የበቆሎ ምርትን በእጥፍ ለማሳደግ መታቀዱን ገልጸዋል። በክረምት እርሻው ላይ የተሰማሩ የወረዳው አርሶ አደሮችም፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከሚረዱ ሰብሎች ጎን ለጎን ከፍተኛ የኢኮኖሚ ጠቀሜታ ያላቸውን ሰብሎችም በትኩረት እንደሚያመርቱ ተናግረዋል።  
በሲዳማ ክልል የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ ለሪፎርም ሥራዎች ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 5, 2026 417
ሀዋሳ፣ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ)፡-የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ ለሪፎርም ሥራዎች ትኩረት መስጠቱን የሲዳማ ክልል ገንዘብ ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ዓላማ ላይ ለባለድርሻ አካላት ያዘጋጀው የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ በሃዋሳ ከተማ ተካሂዷል።   የቢሮው ሀላፊ አቶ ሀይሌ ሀርሲሳ ለኢዜአ እንደገለጹት በቢሮው የመንግስት አገልግሎትን ቀልጣፋ፣ ተደራሽና ፍትሀዊ ለማድረግ የአስተዳደር ሪፎርም ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው። የሪፎርም ሥራው የበጀት ሥራዎችን በቴክኖሎጂ ተደግፎ ለማከናወን ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንም አንስተዋል። ቢሮው የክፍያ ስርዓቱ በኤሌክትሮኒክስ የሚከናወንበትን አሰራር በመዘርጋት አገልግሎቱን ከጥሬ ገንዝብ ንክኪ ነጻ በማድረግ ግልጸኝነትና ተጠያቂነት የማስፈን ሥራ መጀመሩንም ተናግረዋል።   በሲዳማ ክልል ገንዘብ ቢሮ የሪፎርም ቴክኒክ ቡድን አስተባባሪ አቶ ጌቱ በቀለ በበኩላቸው እንዳሉት በቢሮው ቀደም ሲል ይሰጡ የነበሩ አገልግሎቶች በሪፎርሙ ደረጃ ወጥቶላቸው እየተከናወኑ ይገኛሉ። ሪፎርሙ የተቋሙን አሰራር እና የሠራተኛውን የመፈጸም አቅም በማሳደግ የህዝብ ተቀባይነትና አመኔታን ለመፍጠር የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ በገንዘብ ሚኒስቴር የሪፎርም ድጋፍ ቡድን ሀላፊ አቶ ይገዙ ዳባ ናቸው።   ተግባራዊ የሚደረገው የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ለዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ብለዋል።
በፓርኩ ለአቮካዶ ዘይት አምራች ኢንዱስትሪዎች ምርት የሚያቀርቡ ማህበራት ተጠቃሚ ሆነዋል
Jun 5, 2026 472
ሀዋሳ ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦በይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ማቀነባበሪያ ፓርክ ከአምራች ኢንዲስትሪዎች ጋር በተፈጠረላቸው የገበያ ትስስር ተጠቃሚ መሆናቸውን በአቮካዶ ምርት ማቅረብ ሥራ ላይ የተሰማሩ የአርሶ አደር ማህበራት ገለጹ። በይርጋለም ኢንዱስትሪ ፓርክ ከሚንቀሳቀሱ 10 አምራች ኢንዱስትሪዎች አራቱ በአቮካዶ ዘይት ማምረት ሥራ ላይ የተሰማሩ ሲሆን ይህም ለአካባቢው አርሶ አደሮች የገበያ ትስስር በመፍጠር ተጠቃሚ እያደረጋቸው ነው። በተለይም አርሶ አደሩ በሕብረት ሥራ ማህበራት ተደራጅቶ ምርቱን ለኢንዱስትሪዎች እንዲያቀርብ ምቹ ዕድል እየፈጠረ መጥቷል፡፡ አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ማህበራት መካከል የ"ዶንጎራ ቀዋዶ አትክልትና ፍራፍሬ አምራችና አቅራቢ ማህበር" ሰብሳቢ አቶ ላታሞ ያዕቆብ እንደገለጹት፤ ማህበሩ በአምስት መሰረታዊ የሕብረት ሥራ ማህበራት በርካታ አርሶ አደሮችን አቅፎ የአቮካዶ ምርትን ለኢንዱስትሪዎች እያቀረበ ይገኛል።   ይህም ቀደም ሲል አርሶ አደሩ ገበያን በማፈላለግ ያጋጥመው የነበረውን የምርት፣ የጊዜና የጉልበት ብክነት በማስቀረት የተሻለ ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻሉን ተናግረዋል። የማህበሩ አባላት የአቮካዶ ምርታቸውን በማህበሩ በኩል በቀጥታ ለኢንዱስትሪዎች በማቅረብ ገቢያቸውን እያሳደጉ መሆኑንም ገልጸዋል። ሌላው የ”ፋያ ኢንተርፕራይዝ ማህበር” ሰብሳቢ ወጣት ሻላ ካሳ፤ በማህበር ተደራጅተው የአቮካዶ ምርትን በፓርኩ ውስጥ ለሚገኙ ኢንዱስትሪዎች በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን ገልጿል።   በቀን ከ50 ሺህ እስከ 80 ሺህ ኪሎ ግራም የአቮካዶ ምርት ሰብስበው እንደሚያቀርቡ ገልጾ፣ በምርት አሰባሰብ ሂደት ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል ብሏል። አሁን ላይ ገቢና ተጠቃሚነታቸው በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንም ተናግሯል። የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሀይሉ የተራ በበኩላቸው እንዳሉት፤ በአሁኑ ወቅት በፓርኩ በአቮካዶ ዘይት ለተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተደራጅተው ምርት የሚያቀርቡ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ እየሆኑ ነው።   ፓርኩ ወደሥራ ከገባ ያለፉት አምስት ዓመታት ከ83ሺህ ቶን በላይ የአቮካዶ ምርት ለፓርኩ መቅረቡን የጠቆሙት አቶ ሀይሉ፣ ለበርካቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉንም ተናግረዋል። በማህበር ተደራጅተው ለኢንዱስትሪዎቹ የአቮካዶ ምርት የሚያቀርቡ አርሶ አደሮችም ተጠቃሚ እየሆኑ ይገኛሉ ብለዋል። አቶ ሀይሉ እንዳሉት በ43 ማህበራት የተደራጁ ከ132ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ምርታቸውን ለፓርኩ በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ ይገኛሉ፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም