ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በወላይታ ሶዶ ከተማ እየተከናወነ ያለው የወንዝ ዳርቻ ልማት ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩ ባለፈ የሥራ ባህል እያሳደገ ነው
Jun 13, 2026 372
ወላይታ ሶዶ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ በወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር እየተከናወነ የሚገኘው የወንዝ ዳርቻ ልማት የሥራ ዕድል ከመፍጠሩ ባለፈ የሥራ ባህላቸው እንዲቀየር አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተጠቃሚዎች ገለጹ። በከተማዋ ከ200 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ግንባታው እየተፋጠነ ያለው የወንዝ ዳርቻ ልማት የተለያዩ የመዝናኛ ሥፍራዎችን አካቶ እየተገነባ መሆኑም ተመላክቷል።   በልማቱ በሥራ ዕድሉ ተጠቃሚ ከሆኑ ወጣቶች መካከል ኤርሚያስ ዳዊት እና ማለዳ ማቴዎስ በከተማው የተጀመረው የወንዝ ዳርቻ ልማት የከተማዋ ነዋሪዎች በተለያየ መንገድ ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው። በልማቱ የሥራ ዕድል እንደተፈጠረላቸው የተናገሩት ወጣቶቹ፣ በዚህም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ከማሳደግ ባለፈ ምሽት ጭምር በመስራት የሥራ ባህላቸው እየተቀየረ መምጣቱን ተናግረዋል።   ሠርተው በሚያገኙት ገቢ ቤተሰቦቻቸውን እየደገፉና የራሳቸውን ጥሪት ለማፍራት እያገዛቸው መሆኑንም ገልጸዋል።   የወንዝ ዳርቻ ልማቱን እያከናወነ የ ሚገኘው ስራ ተቋራጭ ባለቤት አቶ ከበደ ተካ በበኩላቸው፣ የልማት ስራውን ከተያዘለት ጊዜ አስቀድሞ ለማጠናቀቅ ቀንና ምሽት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በቅንጅት እየተከናወነ ባለው የመጀመሪያ ዙር የወንዝ ዳርቻ ልማት ለ70 ሰዎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸው፣ ልማቱ ትውልድ ተሻጋሪ እንዲሆን በጥራትና በፍጥነት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። የወንዝ ዳርቻ ልማት የከተማውን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ የህብረተሰቡን የሥራ ባህል በማሻሻል ረገድ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ተናግረዋል።   የወላይታ ሶዶ ከተማ ማዘጋጃ ቤት የተቀናጀ መሠረተ ልማት አቅርቦት ሥራ ሂደት አስተባባሪ አስራት ዳዊት በበኩላቸው የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራውን በታቀደለት ጊዜ ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ልማቱ በሁለት ሄክታር ላይ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው አምፊ ቴአትር፣ ፋውንቴኖች፣ ሰው ሰራሽ ሐይቅ፣ የተሽከርካሪ፣ የእግረኛና የብስክሌት መንገድ እንዲሁም የተለያዩ መዝናኛና ማረፊያ ቦታዎች እንደሚኖሩት አስረድተዋል። የሥራ ተቋራጩ በውሉ መሰረት ሥራውን እያከናወነ መሆኑን ጠቁመው፣ ፈጥኖ ለማጠናቀቅም ቀንና ምሽት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ለልማት ሥራው ከ200 ሚሊየን ብር በላይ በጀት የተያዘ ሲሆን ተጠናቅቆ ለአገልግሎት ሲበቃ የከተማዋን ገጽታ እንደሚቀይረው ተናግረዋል። በተጨማሪም የቱሪስት ፍሰትን ለማሳደግ፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ እና የከተማዋን ገቢ ከማሳደግ አንጻር ጠቀሜታው የጎላ በመሆኑ ሥራው በልዩ ትኩረት እየተመራ ይገኛል ነው ያሉት።
የደብረ ማርቆስ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት ከትራንስፖርትም ባለፈ ለንግድና ኢንቨስትመንት ትልቅ አቅም ነው
Jun 13, 2026 222
ደብረ ማርቆስ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ የደብረ ማርቆስ አውሮፕላን ማረፊያ አገልግሎት መጀመር ከትራንስፖርትም ባለፈ ለንግድና ኢንቨስትመንት ትልቅ እንደሚሆን በኢትዮጵያ አየር መንገድ የክልል ኤርፖርቶች ፋሲሊቲ ኃላፊ ተወልደ ግርማይ ገለጹ። አየር መንገዱ ወደ ደብረ ማርቆስ ከተማ የሚያደርገውን የቅድመ ምረቃ በረራ በዛሬው እለት ጀምሯል። ኃላፊው ለኢዜአ እንደገለጹት የደብረ ማርቆስና አካባቢው ህብረተሰብ የቆየ የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ጥያቄ በመንግስት በተሰጠው ትኩረት ምላሽ አግኝቷል። በዛሬው እለትም የቅድመ ምረቃ በረራ መጀመሩን ተናግረው በተለያዩ አካባቢዎች የዜጎችን የመሰረተ ልማትና የአገልግሎት ፍላጎት የማሳለጥ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። አውሮፕላን ማረፊያው አገልግሎት መጀመሩ ለአካባቢው ከትራንስፖርትም ባሻገር ለንግድና ኢንቨትስመንት እንዲሁም ለቱሪዝም ሴክተሩ ትልቅ አቅም መሆኑን ተናግረዋል። የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ስለሺ ተመስገን፤ የደብረ ማርቆስና አካባቢው ህብረተሰብ የአየር ትራንስፖርት የረዥም ጊዜ ጥያቄ ምላሽ በማግኘቱ ትልቅ ደስታ የፈጠረ መሆኑን ገልጸዋል። የትራንስፖርት አገልግሎት መጀመሩም የከተማውንና የአካባቢውን የኢንቨስተመንት፣ የንግድና የቱሪዝም እንቅስቃሴ ለማፋጠን የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል። የምስራቅ ጎጃም ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኑርልኝ ብርሃኑ በበኩላቸው የአየር ትራንስፖርቱ ለዘመናት የነበረውን ፍትሃዊ የልማት ጥያቄ ምላሽ የሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። በበረራው ከተሳተፉት መካከል አቶ ባየ ገሰሰ እና ወይዘሮ ቃልኪዳን በረከት አየር መንገዱ በረራ በመጀመሩ መደሰታቸውን ተናግረዋል። የአካባቢውን ህዝብ የረጅም ጊዜ ጥያቄ መሰረት አድርጎ መንግስት ፈጣን ተግባራዊ ምላሽ በመስጠቱም እናመሰግናለን ብለዋል።
በአማራ ክልል የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ በመቀየር ኢንቨስትመንትና ቱሪዝምን እያነቃቃ ነው
Jun 13, 2026 227
ወልድያ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል እየተካሄደ ያለው የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ በመቀየር ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ዘርፍ መነቃቃት አዲስ ምዕራፍ መክፈቱን የክልሉ ከተማና መሰረት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የአማራ ክልል ከተማና መሰረት ልማት ቢሮ ክልላዊ የኮሪደር ልማት ልምድ ልውውጥና የግምገማ መድረክ በወልድያ ከተማ ተካሂዷል። የቢሮ ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ እንደገለጹት የክልሉ ከተሞችን ለነዋሪዎች፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በተለይም የመኪና፣ የብስክሌትና የእግረኛ መንገድ እንዲሁም የመዝናኛ የአረንጓዴ ስፍራና ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን አካቶ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴን ለማፋጠን መሰረት እየጣለ ነው ብለዋል። የኮሪደር ልማት በተካሄደባቸው አካባቢዎች ጠንካራ የቢዝነስና የኢንቨስትመንት ማዕከላት መፈጠራቸውን ገልጸው፤ ይህም ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት መነቃቃት ታላቅ ተስፋ ይዞ መጥቷል ብለዋል። ባዛሬው የልምድ ልውውጥና የግምገማ መድረክም የተሻለ የሰሩ ከተሞች ለሌሎች ልምዳቸውን በማካፈል በቀጣይ ከተሞች ተቀራራቢ እድገት እንዲያስመዘገቡ ያለመ መሆኑን አስረድተዋል። በብልጽግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርጫት ጽህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ፍስሃ ደሳለኝ በበኩላቸው ከተሞችን በኮሪደር ልማት ለማስዋብና ገጽታቸውን ለመቀየር የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል ብለዋል። ልማቱ የከተሞችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቀስቃሴ ከማሳደግ ባለፈ የገጠሩን እድገት ለማፋጠን እንደሚያስችለም አመልክተዋል። የባህር ዳር ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ አስሜ ብርሌ በበኩላቸው፣ በባህር ዳር የተገነባው የኮሪደር ልማት የጣና ሐይቅን ጸጋ የገለጠና የከተማዋን ውበት ይበልጥ ያደመቀ መሆኑን ተናግረዋል። የኮሪደሩ ልማቱ የተሽከርካሪ፣ የሳይክልና የእግረኛ መንገድ፣ የመዝናኛ ስፍራ፣ የአረንጓዴ ሰፍራና ሌሎች ልማቶችን ማካተቱን ጠቁመው ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል። በጎንደር ከተማ አስተዳደር የከተማና መሰረት ልማት መምሪያ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሙሉጌታ ታደሰ በጎንደር የተከናወነው የኮሪደር ልማት ለቱሪዝም እንቅስቃሴና ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ብለዋል። በተለይ የፋሲል ግንብን፣ የሰሜን ተራሮችንና ሌሎች የመስህብ ስፍራዎችን ሊጎበኙ የሚመጡ የውጭና የአገር ውስጥ ቱሪስቶችን የቆይታ ጊዜ በማራዘም አዎንታዊ ለውጥ አምጥቷል ብለዋል። ልማቱ የቀጣዩን ትውልድ እድገት ጭምር መሰረት ያደረገ መሆኑን ጠቁመው "መድረኩም ልምዳችንን ለሌሎች ከተሞች ለማጋራትና ክፍተታችን ለመሙላት ያስቻለ ነው" ብለዋል። በኮሪደር ልማት ደሴ ከተማን ማስዋብና ማሳመር ተችሏል ያሉት ደግሞ የደሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሞላልኝ ናቸው። በመድረኩ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር)ን ጨምሮ የክልል፣ የከተማና የዞን አመራሮች ተሳትፈዋል።
በክልሉ ከ3 ነጥብ 6 ሚሊየን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ ተሰራጭቷል
Jun 13, 2026 238
ባህር ዳር፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ለመኸር ሰብል ልማት ከ3 ነጥብ 6 ሚሊየን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ በማሰራጨት ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የግብርና ግብዓትና ሜካናይዜሽን ዳይሬክተር ወይዘሮ ሙሽራ ሲሳይ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በክልሉ በ2018/2019 የምርት ዘመን ምርታማነትን ለማሳደግ ግብዓትን ለአርሶ አደሩ በወቅቱ የማቅረብ ሥራ እየተሰራ ነው። ለምርት ዘመኑ 8 ነጥብ 6 ሚሊየን ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ለማቅረብ ታቅዶ እስካሁን ከ4 ሚሊዮን 822 ሺህ ኩንታል ማዳበሪያን ወደ ክልሉ በማጓጓዝ ለአርሶ አደሩ የማሰራጨት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። እስካሁንም ከ3 ነጥብ 6 ሚሊየን ኩንታል በላይ የሚሆነው እንደተሰራጨ የገለጹት ዳይሬክተሯ፤ የማዳበሪያ አቅርቦቱ ተጠናክሮ መቀጠሉንም ጠቁመዋል። ከዚህ በተጨማሪም በምርት ዘመኑ 220 ሺህ ኩንታል የተለያዩ የሰብል ምርጥ ዘር ለማቅረብ በታቀደው መሰረት እስካሁን 137 ሺህ 675 ኩንታል ለአርሶ አደሩ ደርሷል ብለዋል። የማዳበሪያና የምርጥ ዘር አቅርቦቱ በወቅቱ መካሄዱ አርሶ አደሩ ምርታማነቱን በማሳደግ የምግብ ዋስትናውን ከማረጋገጥ ባሻገር ለገበያ የሚተርፍ ምርት በአይነት፣ በብዛትና በጥራት እንዲያመርት አዎንታዊ ሚና እንደሚጫወትም አመልክተዋል። "በመኸር ምርቱ ምንም አይነት የግብዓት አቅርቦት ችግር እንዳያጋጥም እየተሰራ ነው" ያሉት ወይዘሮ ሙሽራ፣ አስፈላጊውን ግብአት ለማቅረብ በየደረጃው በቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። በደቡብ ጎንደር ዞን ፋርጣ ወረዳ ማይነት ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ንጋቴ ጎሸ እንደገለጹት ለዘር የሚያስፈልጋቸውን አምስት ኩንታል ማዳበሪያ ቀድሞ ማግኘታቸው የዘር ሥራቸውን ያለምንም ችግር ለማከናወን አግዟቸዋል። በሰሜን ጎጃም ዞን የሰሜን ሜጫ ወረዳ እንጉቲ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ስሜነህ አበረ በበኩላቸው፤ የዘንድሮው የግብርና ግብዓት አቅርቦት ወቅቱን ጠብቆ መከናወኑን ተናግረዋል። ይህም የዘር ሥራቸውን ፈጥነው በማከናወን የተሻለ ምርት እንዲያገኙ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ነው ያስታወቁት። በአማራ ክልል በመኸር ወቅት 5 ነጥ 6 ሚሊየን ሄክታር የሚጠጋ መሬት በማልማት ከ205 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደስራ መገባቱን ከቢሮው የተገ መረጃ ያስረዳል።    
በክልሉ ስልጤ እና ሀላባ ዞኖች በመኸር ወቅት ከ132 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ ይለማል
Jun 13, 2026 94
ወራቤ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስልጤ እና ሀላባ ዞኖች በ2018/19 የመኸር ወቅት ከ132 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ በተለያዩ ሰብሎች እንደሚለማ ተገለጸ። በመኸር እርሻ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የዞኖች ግብርና መምሪያዎች እንደገለጹት ለመኸሩ የግብርና ልማት ሥራ አስፈላጊውን የግብርና ግብአት በማሟላት የሰብል ልማት ስራዎችን ለማከናወን ታቅዶ ወደተግባር ተገብቷል። የስልጤ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሙበራ ከማል እንደገለጹት በዞኑ በ2018/19 በመኸር ወቅት የግብርና ልማት ሥራ ከ104 ሺህ 380 ሄክታር በላይ ማሳ በተለያዩ ሰብሎች ይሸፈናል። በአዝርዕትና በሆልቲካልቸር ሰብሎች ከሚለማው መሬትም ከ5 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ግብ ተጥሎ ወደ ተግባር መገባቱን ጠቁመዋል። ለመኸር ወቅት የግብርና ልማት ሥራ ከ306 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለማሰራጨት ታቅዶ 141 ሺህ 387 ኩንታል ማሰራጨት መቻሉን ጠቅሰው፣ ቀሪውንም በቀጣይ ጊዜያት የማሰራጨት ሥራ እይከናወናል ብለዋል። በዞኑ በመኸር ወቅት ከሚለማው ማሳ አብዘኛው በሜካናይዜሽን እርሻ ትራክተር በመጠቀም በክላስተር እንደሚለማ ጠቁመው፤ ይህም አቅምን አሟጦ በመጠቀም ውጤታማ ለመሆን ያግዛል ብለዋል። በተመሳሳይ የሀላባ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የዞኑ ግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ ሀጂ ኑርዬ በበኩላቸው እንዳሉት በዞኑ ለመኸር ወቅት ግብርና ልማት አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራ እየተከናወነ ነው። በዘንድሮ የመኸር ወቅት ከ28 ሺህ 140 ሄክታር በላይ ማሳ በተለያዩ ሰብሎች በማልማት ከ1 ሚሊዮን 546 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ግብ ተጥሎ ወደ ተግባር ተገብቷል ብለዋል። ለዚህም ስኬት ከ130 ሺህ 200 ኩንታል በላይ የዳፕና ዩሪያ ማዳበሪያን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ ግብአቶችን የማሰራጨት ሥራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።  
በምዕራብ ሸዋ ዞን የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ለንብ ማነብ ስራ ምቹ ሁኔታ በመፈጠሩ የማር ምርት እያደገ መጥቷል
Jun 13, 2026 129
አምቦ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ ዞን ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራዎች ለንብ ማነብ ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩ የማር ምርት እያደገ መምጣቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በጽህፈት ቤቱ የንብና ሐር ልማት ባለሙያ የሆኑት ብርሃኑ ለችሳ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በዞኑ የንብ ማነብ ዘርፉን ለማዘመን በየደረጃው በተደረገው ሰፊ ጥረት የማር ምርቱን ማሳደግ ተችሏል። በተለይም በዞኑ በሚገኙ 23 ወረዳዎች በተካሄደው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ለንብ ማነብ ስራ ምቹ ሁኔታ በመፈጠሩ፣ በርካታ ወጣቶች በዘርፉ ተሰማርተው ውጤታማ እየሆኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። የማር ምርቱን ይበልጥ ለማሳደግ ለአርሶ አደሮች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ከመስጠት ባለፈ ዘመናዊ የንብ ቀፎዎች መሰራጨታቸውን ጠቁመው ባለሀብቶችም በዘርፉ እንዲሰማሩ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል።   ይህም በዘርፉ ለተሰማሩ 200 ሺህ አርሶ አደሮች ተጨማሪ ገቢ ከመፍጠሩ በላይ፣ ህብረተሰቡ ጥራቱን የጠበቀ ምርት በገበያ ላይ እንዲያገኝ አስችሏል ብለዋል። በ2018 በጀት ዓመት 10 ሺህ 340 ቶን ማር ለማምረት ታቅዶ የነበረ ሲሆን፣ ባለፉት 11 ወራት ዕቅዱን ሙሉ በሙሉ ማሳካት ተችሏል ነው ያሉት። ይህ ምርት የተሰበሰበው ከ851 ሺህ በላይ ከሚሆኑ ባህላዊ፣ የሽግግርና ዘመናዊ የንብ ቀፎዎች መሆኑን ጠቅሰው፣ የተገኘው የማር ምርት ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ220 ቶን ዕድገት አሳይቷል ብለዋል።
ሀዋሳን የቱሪዝም እና ኢንቨስትመንት ማዕከል የማድረግ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jun 13, 2026 108
ሀዋሳ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ ሀዋሳ ከተማን በማልማት የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ማዕከልነቷን ይበልጥ ለማሳደግ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ አስታወቁ። የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ተካሂዷል።   በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ የተገኙት ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ መንግስት ከተሞችን ለኑሮ ምቹና ተስማሚ ለማድረግ ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል የኮሪደርና የመዳረሻ ስፍራዎች ልማት ተጠቃሽ ናቸው። በሀዋሳ ከተማ በተከናወነው የኮሪደር ልማት የከተማዋን የተፈጥሮ ውበት ይበልጥ አጉልቶ ማውጣት ተችሏል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በዚህ ወቅት የሀዋሳ ፍቅር ሐይቅን ለማልማት በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የሐይቅ ዳርቻ ልማቱ የሀዋሳ ብቻ ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያውያን በመሆኑ፣ ሁሉም አካላት ለስኬቱ እንዲረባረቡ ርዕሰ መስተዳድሩ ጥሪ አቅርበዋል።   በሐይቅ ዳርቻ ልማቱ ከሚገነቡ የመዝናኛ ማዕከላት በተጨማሪ፣ ዘመናዊ የትራንስፖርትና የመዝናኛ ጀልባዎችን በማስመጣት ባለሀብቶች እንዲሳተፉም ጋብዘዋል። በተጨማሪም በሀገር ውስጥና ከሀገር ውጪ የሚገኙ የሀዋሳ ወዳጆች ለፕሮጀክቱ ስኬት የበኩላቸውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል።   የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው፣ የሐይቅ ዳርቻ ልማቱ ከተማዋን ከብክለት ጠብቆ ለመጪው ትውልድ ለማውረስ የዲዛይን ስራ ተጠናቆ ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል። በከተማዋ እስካሁን ከ10 ኪሎ ሜትር በላይ የኮሪደር ልማት የተከናወነ ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት ተጨማሪ 3 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር የማልማት ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በአጠቃላይ 12 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የሐይቅ ዳርቻ ልማት የከተማዋን ውበት ከማሳደግ ባለፈ፣ ኑሯቸውን በአሳ ማስገር ስራ ላይ የመሰረቱ ነዋሪዎችን ህይወት ለመለወጥ ታስቦ የተዘጋጀ ነውም ብለዋል። ዛሬ የዚህ ፕሮጀክት የመጀመሪያ ዙር በይፋ የተጀመረ ሲሆን፣ ፕሮጀክቱን በስድስት ወር ውስጥ ለማጠናቀቅ ይሰራል ነው ያሉት። ፕሮጀክቱ ዘመናዊ ሬስቶራንቶችና ሱቆችን፣ ዘመናዊ መሠረተ ልማቶችን፣ የመመልከቻ ማማዎችና የአሳ ማስገሪያ ስፍራዎችን፣ የህዝብ መሰብሰቢያ ሰገነቶችን፣ የጎርፍ ውሃ ማጣሪያ ስርዓትን እንዲሁም የሐይቅ ዳርቻ የብስክሌትና የእግረኛ መንገዶችን ያካተተ መሆኑ ተገልጿል።
የሌማት ትሩፋት የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታችንን እያሳደገ ነው - ተጠቃሚዎች
Jun 13, 2026 104
አርባ ምንጭ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ የሌማት ትሩፋት መርሃግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደገ መምጣቱን በአርባ ምንጭ ከተማ የመርሃ-ግብሩ ተጠቃሚዎች ገለጹ። በአርባ ምንጭ ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው የመርሃ-ግብሩ ተጠቃሚዎች መርሀግብሩ የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ጥሪት ለማፍራት እንዳገዛቸው ነው የገለጹት። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል የ"እስታኒያ ዶሮ እርባታ ማህበር" ሰብሳቢ ወጣት አዲስዓለም ደሴ ማህበሩ በ200ሺህ ብር ካፒታል 180 የሥጋና የእንቁላል ጣይ ዶሮዎችን በማርባት ወደ ሥራ መግባቱን አስታውሳለች። በአምስት አባላት ሥራውን የጀመረው ማህበሩ፣ የዕንቁላልና የሥጋ ዶሮዎችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ በማቅረብ በገበያ ማረጋጋት ሥራው የራሱን አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ተናግራለች። መንግስት የእርባታ ቦታ ከማመቻቸት በተጨማሪ በየጊዜው ሙያዊ ድጋፍ ማድረጉ ማህበሩ ውጤታማ እንዲሆን አግዟል። በዚህም የማህበሩ ካፒታል በአጭር ጊዜ ውስጥ ከ700ሺህ በላይ መድረሱን ጠቅሳ፣ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የህብረተሰቡን የአመጋገብ ዘይቤ እየቀየረ መምጣቱንም ገልጻለች። የ"ቤተሰብ እንስሳት እርባታ ማህበር" ሰብሳቢ ቃለአብ ዳኛቸው በበኩሉ የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር በአጭር ጊዜ ውስጥ ከድህነት ለመውጣት አስችሎናል ብሏል። ሥራቸውን ከአራት ዓመት በፊት በቀን 6 ሊትር ወተት በሚሰጡ አምስት የአካባቢው ዝርያ ላሞች እንደጀመሩ ገልጾ፣ በሂደት ሙሉ ለሙሉ በተሻሻሉ የላም ዝርያዎች በመተካት ምርታማነታቸውን መሳደጋቸውን ተናግሯል። በዚህም ካፒታላቸው እያደገ መምጣቱንና ለሰባት ሰዎችም የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ያመለከተው ወጣቱ፣ የወተት ምርታቸውን ለአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪዎች እያቀረቡ መሆናቸውን አስታውቋል። በአሁኑ ወቅት የወተት ላሞች ቁጥር 15 መድረሱን ገልጾ በየዕለቱ ከእያንዳንዳቸው 30 ሊትርና ከዚያ በላይ የወተት ምርት እንደሚያገኙ ጠቁሟል። የአርባ ምንጭ ከተማ ግብርና መምሪያ ሃላፊ መተኪያ አበበ የሌማት ትሩፋት የምግብ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥ፣ የኢኮኖሚ ዕድገት እና የዜጎችን የኑሮ ደረጃ የሚያሻሽል መርሀ ግብር መሆኑን አንስተዋል። በመርሃ ግብሩ የዜጎችን የምግብ ዋስትና በማጠናከርና የቤተሰብ ገቢን በማሻሻል በኩል ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸው፣ በተለይ በሕጻናትና በእናቶች ይስተዋሉ የነበሩ የሥነ ምግብ ችግሮችን ለመቀነስ ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል ብለዋል። በከተማው የዶሮ፣ የንብ፣ የዓሣ፣ የወተት እና የሥጋ መንደሮች የተቋቋሙ ሲሆን፣ በዘርፉ የተሰማሩ ዜጎችም ውጤታማ እንዲሆኑ አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
አዲስ አበባ የዓለም አቀፍ ውድድሮች ቀዳሚ ተመራጭ ከተማ
Jun 13, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ አዲስ አበባ አህጉራዊና ዓለም አቀፍ የስፖርት ውድድሮች በስፋት የሚስተናገዱባት ቀዳሚ ተመራጭ መሆን መቻሏን የከንቲባ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለስፖርቱ ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረትና ባከናወናቸው ግዙፍ የስፖርት መሠረተ ልማት ግንባታዎች ተመራጭ የስፖርት ማዕከል መሆን መቻሏን አመልክቷል። ባለፉት ዓመታት በከተማዋ የተገነቡት ከ1,580 በላይ የሕዝብና የወጣቶች ስፖርት ማዕከላት ማኅበረሰባዊ ተሳትፎን ከማሳደግ ባለፈ አገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ውድድሮችን ለማስተናገድ ትልቅ መሠረት መሆኑን ገልጿል።   በቅርቡ በታላቅ ድምቀት የተጠናቀቀውና በመስቀል አደባባይ የተካሄደው 19ኛው የኢትዮጵያ ግማሽ ማራቶንን ጨምሮ ከተማዋ የተለያዩ ዓለም አቀፍ የብስክሌት፣ የአትሌቲክስ፣ የጎዳና ላይ ሩጫን ጨምሮ ሌሎች የስፖርት ሁነቶችን በስኬት በማስተናገድ መዲናዋ ምቹ ፥ እና ተመሪጭ ከተማ መሆኗን በተግባር እያሳየች ትገኛለች። አዲስ አበባ አሁን ላይ የስፖርት ልሂቃን መገናኛ ትላልቅ ውድድሮችንና ደጋፊዎችን የምታስተናግድ ደኅንነቷ የተጠበቀና ውብ መዲና ሆናለች ሲል ጽህፈት ቤቱ ገልጿል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በከተማ አስተዳደሩ የተከናወኑት የተቀናጁ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች፣ የወንዝ ዳርቻዎች እና ደረጃቸውን የጠበቁ የስፖርት ማዕከላት መስፋፋት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለስፖርት ቱሪዝም ዕድገት ትልቅ አቅም ፈጥረዋል። ይህ የስፖርት ቱሪዝም ዕድገት ከስፖርታዊ ፋይዳው ባሻገር፣ ለሆቴል ኢንዱስትሪው፣ ለትራንስፖርት ዘርፉና ለአካባቢው አነስተኛና ጥቃቅን የንግድ አንቀሳቃሾች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ መነቃቃትን መፍጠሩ ተመላክቷል። ይህም የከተማ አስተዳደሩ የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ የያዘውን ግብ በከፍተኛ ደረጃ እየደገፈው እንደሚገኝም ነው ጽሕፈት ቤቱ ያስታወቀው።
በቆላማ አካባቢዎች የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ ውጤታማ የውሃና መስኖ ፕሮጀክቶች ዕውን እየሆኑ ነው
Jun 13, 2026 72
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ በቆላማ አካባቢዎች የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ ውጤታማ የውሃና መስኖ ፕሮጀክቶች ዕውን እየሆኑ እንደሚገኝ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ገለጸ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ በቦረና ዞን ባደረጉት ጉብኝት እንዳሉት፤ እንደ ቦረና ባሉ ቆላማ አካባቢዎች የተገነቡ የመስኖ ፕሮጀክቶች የአየር ንብረት ለውጥን በመቋቋም የውሃ መሠረተ ልማትን ለማረጋገጥ ትልቅ ምዕራፍ ከፍቷል፡፡ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ አነስተኛ፣ መካከለኛና ከፍተኛ የውሃና መስኖ መሰረተ ልማት እየተገነቡ ይገኛል። በመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የቆላማ አካባቢ ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ ሰይድ ዑመር ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የድርቅ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል አቅም እየፈጠረች ነው።   በሀገር አቀፍ ደረጃም የአርሶና አርብቶ አደሩን የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ በሁለት ምዕራፍ የተቀረጹ የኑሮ ማሻሻያ ስትራቴጂክ ፕሮጀክቶች እየተገነቡ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የአርሶና አርብቶ አደሩን የአየር ንብረት ለውጥ የድርቅ ተጋላጭነት የሚቀነስ የውሃና መስኖ የልማት ፕሮጀክቶች ዕውን እንዲሆኑ እያደረገ ነው ብለዋል። በመጀመርያ ምዕራፍም በሰባት ክልሎች በሚገኙ መቶ ወረዳዎች የውሃ፣ መስኖ፣ መኖና አማራጭ ገቢ ማስገኛ ፕሮጀክቶችን በመገንባት 2 ነጠብ 9 ሚሊየን ዜጎች ተጠቃሚ መደረጋቸውን ተናገረዋል። የተጠናቀቁት 218 ስትራቴጂክ ፕሮጀክቶችም አንድ መቶ ሥድስቱ የውሃ፤ አስራ አንዱ ደግሞ ከ2 ሺህ ሔክታር መሬት በላይ ማልማት የሚያስችሉ የመስኖ ፕሮጀክቶች መሆናቸውን አስታውቀዋል። በእንስሳት ሃብት ላይ የሚደርሰውን ተፅዕኖ ለመቀነስም ከ217 ሺህ ቶን በላይ መኖ ማልማት የሚያስችሉ ፕሮጀክቶች እውን መሆናቸውን አንስተዋል። በሁለተኛው ምዕራፍም ከልማት አጋሮች የተገኘን 424 ሚሊየን ዶላር የገንዘብ ድጋፍ ድርቅና ድንገተኛ አደጋን ምላሽ የሚሰጡ ፕሮጀክቶችን ለመገንባት ወደ ተግባር ተገብቷል ብለዋል። በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት በስምንት ክልሎች በሚገኙ 120 ወረዳዎች የድርቅና ድንገተኛ አደጋ ምላሽ ሰጪ የውሃና መስኖ ፕሮጀክቶች በግንባታ ላይ እና ለግንባታ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በተጨማሪም በሀገር አቀፍ ደረጃ በአማራጭ ገቢ ማስገኛ ፕሮጀክቶች በርካታ ወጣቶች ተደራጅተው ተጠቃሚ እንዲሁኑ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የአስደናቂ ባህል፣ ታሪክና ቅርስ ባለቤት ሀገር መሆኗን በጉብኝታችን አረጋግጠናል
Jun 13, 2026 91
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአስደናቂ ባህል፣ ታሪክና ቅርስ ባለቤት ሀገር መሆኗን በጉብኝታቸው ማረጋገጣቸውን በአዲስ አበባ የሚገኙ የዲፕሎማቲክ እግር ኳስ ቡድን አባላት ገለጹ፡፡ የመዲናዋን ገጽታና የቱሪዝም መዳረሻዎቿን ለዓለም በማስተዋወቅ ስፖርት ያለው ሚና የላቀ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ቱሪዝም ኮሚሽን አስታውቋል፡፡ የ2026ቱ የዓለም ዋንጫ መጀመሩን ምክንያት በማድረግ በአዲስ አበባ የሚገኙ የተለያዩ ሀገራት ኤምባሲዎችና ዓለም አቀፍ ተቋማት የተሳተፉበት የዲፕሎማቲክ እግር ኳስ ውድድር ተዘጋጅቷል። በውድድሩ የሚሳተፉ የዲፕሎማቲክ እግር ኳስ ቡድን አባላት እንዲሁም የውድድሩን ዋንጫ አዘጋጅተው ያመጡ የሀገራት እንግዶች በከተማዋ የሚገኙ ዋና ዋና የቱሪስት መስህቦችን ጎብኝተዋል፡፡ እንግዶቹ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም፣ በዓድዋ ድል መታሰቢያ እና በአዲስ ስፖርት ፓርክ ባደረጉት ቆይታ የሀገሪቱን እምቅ ባህል፣ ታሪክና ቅርሶች መመልከታቸውን ገልጸዋል፡፡ በጉብኝቱ ወቅት አስተያየታቸውን የሰጡን ከእንግሊዝ የመጡት ማርክ ሃዬስ ጉብኝቱ ስለ ኢትዮጵያ ብዙ አዳዲስ ነገሮችን እንዲያውቁ እንደረዳቸው ተናግረዋል፡፡ ከእንግሊዝ እግር ኳስ ማህበር ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ የመጡት ጎርዶን ጆንሶን በበኩላቸው በኢትዮጵያ በተመለከቱት የህዝብ ለህዘብ ትስስር፣ መስተጋብር፣ መከባበርና የእንግዳ አቀባበል ባህል መደነቃቸውን ገልጸዋል። በብሔራዊ ሙዚየም የተመለከቱት ቅርስ ኢትዮጵያ ጥንታዊት ሀገር ብቻ ሳትሆን የሰው ዘር መገኛነቷን ያረጋገጡበት መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ በአዲስ አበባ በሚገኘው የተባበሩት መንግስታት የምግብና ግብርና ተቋም ሠራተኛ የሆነው ኡጋንዳውው ጆሴፍ ኪሩሌ፤ ከጉብኝቱ ኢትዮጵያ ታሪክ፣ የሰው ዘር መገኛነትና ወራሪ ኃይልን ድል ስላደረገችበት የአሸናፊነት ታሪክ ጠቃሚ እውቀት ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ የቀኝ ገዥዎችን ምኞት ያከሸፈች አኩሪ ታሪክ ያላትና በአሁኑ ወቅትም በከፍተኛ የዕድገት ጎዳና ላይ የምትገኝ ሀገር መሆኗን መታዘቡን የገለፀው ከካሜሮን የመጣው ሎይስ ኮቫሞ ነው። የአዲስ አበባ ከተማ ቱሪዝም ኮሚሽን የዲጂታል ማርኬቲንግና ፕሮሞሽን ዳይሬክተር ፍሬሕይወት ገብረመድን በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ አዲስ አበባ ዓለም አቀፍና አህጉራዊ ኹነቶች በድምቀት እያስተናገደች ትገኛለች ብለዋል። በዚህም ለተለያዩ ስብሰባዎችና ኮንፍረንሶች ወደ መዲናዋ ለሚመጡ እንግዶች የከተማዋን ገጽታና ሰው ሰራሽ እንዲሁም ታሪካዊ መስህቦች ማስተዋወቅ ለሀገሪቱ ሁለንተናዊ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡ ስፖርት ቱሪዝም ንቁና ጠንካራ ዜጋ ከመፍጠር ባለፈ፣ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎችን በማገናኘት የህዝብ ለህዘብ ትስስርን እንደሚያጠናክርና የመዲናዋን ገጽታ ለዓለም ለማስተዋወቅ የላቀ ሚና እንዳለው አብራርተዋል፡፡ ኮሚሽኑ ይህንን ታሳቢ በማድረግ ያዘጋጀው የዲፕሎማቲክ እግር ኳስ ውድድርና የጉብኝት መርሃ ግብርም የዚሁ ታላቅ ዓላማ አካል መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የወልድያ ከተማ የልማት ስኬት ለሌሎች ከተሞች በጥሩ ማሳያነት የሚጠቀስ የልማት ትጋትና ቁርጠኝነት ማሳያ ነው
Jun 13, 2026 159
ወልድያ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ የወልድያ ከተማ የልማት ስኬት ለሌሎች ከተሞችም በጥሩ ማሳያነት የሚጠቀስ የልማት ትጋትና ቁርጠኝነት ማሳያ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር) ገለጹ። የአማራ ክልል ከተማና መሰረት ልማት ቢሮ ክልላዊ የኮሪደር ልማት የልምድ ልውውጥ እና የግምገማ መድረክ በወልድያ ከተማ እያካሄደ ነው። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ(ዶ/ር) በመድረኩ ላይ እንደገለጹት በክልሉ ከተሞችን በማልማት፣ በማስዋብና በማሳመር ለኑሮ፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ የማድረግ ተግባር እየተከናወነ ነው። በዚህም በኮሪደር ልማትና በሌሎችም ልማቶች ተስፋ ሰጭ ውጤት መመዝገቡን ጠቁመው፣ ህብረተሰቡም ተጠቃሚ እየሆነ ነው ብለዋል። በተለይ የወልድያ ከተማ ችግሮችን ተቋቁማ አስደናቂ ልማት ማከናወን መቻሏ ለሌሎች ከተሞች የልምድና የተሞክሮ ማዕከል መሆን ችላለች ብለዋል። የከተማዋ የልማት ስኬት ለሌሎች ከተሞችም በጥሩ ማሳያነት የሚጠቀስ የልማት ትጋትና ቁርጠኝነት ማሳያ ነው ሲሉ ገልጸዋል። ከከተማዋ አስተዳደር የልማት ቁጭት በመማር ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት ስራዎች ላይ አተኩሮ መስራት ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል። የዛሬው መድረክም የተሻለ የሰሩ ከተሞች ልምዳቸውን በማካፈል ሌሎች እንዲማሩና እንዲነቃቁ ማስቻል ነው ብለዋል። የወልድያ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራሬ በበኩላቸው ከህብረተሰቡ ጋር የከተማውን ሰላም በመጠበቅ ህዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ልማቶችን ማከናወን ተችሏል ብለዋል። በተለይም ከተማዋ በሚፈለገው ልክ አለመልማቷ የፈጠረብን ቁጭት፣ አልህና ጽናት በተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ አስችሎናል ብለዋል። ወልድያ አሁን እየተሞሸረች፣ የእየደመቀችና ለሁሉም ምቹ እየሆነች ትቀጥላለች ሲሉም አመላክተዋል ። ለተሞክሮ የሚሆን ተጨባጭ ውጤት ብናስመዘግብም ገና ስለሚቀረን ልማቱን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። በመድረኩ በአማራ ክልል የ40 ከተሞች ከንቲባዎች እና የመሰረት ልማት ሥራ አስኪያጆችን ጨምሮ ሌሎችም ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።
የሀዋሳ ሀይቅ ዳር ልማት ፕሮጀክት የተለያዩ መሰረተ ልማቶችን አሰናስሎ ሊገነባ ነው
Jun 13, 2026 145
ሀዋሳ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ የሀዋሳ የሀይቅ ዳር ልማት ፕሮጀክት የተለያዩ መሰረተ ልማቶችን አሰናስሎ ሊገነባ መሆኑን የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ። በ3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር የሚከናወነው የሀይቅ ዳር ልማት ፕሮጀክት ማስጀመሪያ መርሐ ግብር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በሀዋሳ ፍቅር ሀይቅ ዳርቻ በመካሄድ ላይ ይገኛል። የሀዋሳ የሀይቅ ዳር ልማት ፕሮጀክት በመጀመሪያው ምዕራፍ የፍቅር ሀይቅ፣ አሞራ ገደል፣ አሳ ገበያን የያዘ ሲሆን በዛሬው እለት በይፋ ስራ የሚጀምረው ሀይቅ ዳርቻ ልማት ትልቁ የመዝናኛ ማዕከል መሆኑ ተገልጿል። በፕሮጀክቱ ዙሪያ ኢዜአ ያነጋገራቸው በሀዋሳ ከተማ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ሃላፊ ኢንጅነር ቸርነት ፍላቴ፤ የፕሮጀክቱ ግንባታ የተለያዩ መገልገያዎችን ያካተተ መሆኑን አስረድተዋል። የፕሮጀክቱ ግንባታ ሬስቶራንቶች፣ ሱቆች፣ የመመልከቻ ማማዎች፣ የዓሳ ማስገሪያ፣ የህዝብ መሰብሰቢያ፣ ሰገነቶች፣ የጎርፍ ውሀ ማጣሪያ፣ የሀይቅ ዳርቻ የብስክሌና የእግረኛ መንገዶች እንዲሁም ሌሎችን ያካተተ መሆኑን ተናግረዋል። የሀይቅዳርቻ ልማት ፕሮጀክቱም በስድስት ወራት በጥራት ተገንብቶ ለአገልገሎት የሚበቃ ሲሆን በግንባታው ከ1 ሺህ ለሚልቁ ዜጎች የስራ ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም አንስተዋል። ከጥቁር ውሀ እስከ ታቦር ተራራ 12 ኪሎ ሜትር ርዝመት የሚሸፍን የሀይቅ ዳርቻ ልማት የሚከናወን መሆኑንም ጠቅሰዋል። በማስጀመሪያ መርሀ ግብሩ ላይ የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጥራቱ በየነ፣ ሌሎች የክልሉና የከተማዋ ከፍተኛ አመራሮች፣ ባለሃብቶች፣ ባለሙያዎችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተገኝተዋል።
የተቋማት እመርታ፤ ከመደበኛ አገልግሎት እስከ ከተማ ግብርና ስኬት
Jun 13, 2026 197
ባለፉት ዓመታት እየተተገበረ ያለው የከተማ ግብርና ምርታማነትን በማሳደግና የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ተጨባጭ ለውጦችን እያስመዘገበ ይገኛል። የከተማ ግብርናን ተግባራዊ ያደረጉ የትምህርት እና የጤና ተቋማትም ዘርፉ ዘርፈ-ብዙ ጥቅሞችን እያስገኘላቸው መሆኑን ለኢዜአ የገለጹ ሲሆን፤ ዋና ግቡም የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ማሳከት ነው፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ በርካታ ተቋማት ወደ አምራችነት በመሸጋገራቸው፣ መርሃ ግብሩ ለዜጎች በተመጣጣኝ ዋጋ ምርትን ተደራሽ ከማድረግ አንጻር አበረታች ድሎችን እያስመዘገቡ ይገኛል፡፡   በዚህም የአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የኮልፌ ጤና ጣቢያ ዋና ስራ አስኪያጅ የትምወርቅ ወልደዮሃንስ እንደገለጹት፤ በተቋሙ የከተማ ግብርና የተጀመረው ዝቅተኛ ተከፋይ የሆኑ ሰራተኞችን በማሰባሰብ፣ በዶሮ እርባታ እና በጎሮ አትክልት ልማት ላይ ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር ነው። በአሁኑ ወቅት ከ1 ሺህ በላይ ዶሮዎችን በማርባት በቀን ከ800 በላይ እንቁላል እየተመረተ መሆኑን ጠቅሰው ምርቶቹን ለተቋሙ ሰራተኞችና ለአካባቢው ህብረተሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ገቢ በማግኘት ላይ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ጤና ጣቢያው ህክምና ከመስጠት ባለፈ፣ ወደ ተቋሙ የሚመጡ የምግብ እጥረት ያለባቸውን ህጻናት በመለየት ለወላጆችም በተግባር የተደገፈ የግንዛቤ ስራ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።   በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 የሚገኘው የሚሊኒየም አጠቃላይ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር ሉዑልሰገድ ይፋሩ፤ የከተማ ግብርና በትምህርት ቤት ውስጥ መተግበሩ ለተማሪዎች ተግባር-ተኮር የሆነ የመማር ማስተማር ሂደት ለመስጠት ማስቻሉን ገልጸዋል። በተጨማሪም በትምህርት ቤቱ የሚመረቱ የግብርና ምርቶች ዝቅተኛ ተከፋይ የሆኑ ሰራተኞች ለገበያ አቅርበው ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኙ እያደረገ መሆኑን አብራርተዋል።   ሌላኛው አስተያየት ሰጪ መምህር ረታ ብርሃኑም፤ ተግባሩ ተማሪዎች ስለ ግብርና እና ውጤቶቹ ከመሰረቱ እንዲረዱ ለማድረግ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አረጋግጠዋል። በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር መሐመድ ሊጋኒ በበኩላቸው ባለፉት የለውጥ ዓመታት የሌማት ቱርፋት መርሀ ግብር ተግባራዊ መደረጉ የከተማ ግብርና ስራ በአዲስ አበባ በስፋት የሚከናወንበትን ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም በከተማው ከ2 ሺህ 700 በላይ በሚሆኑ ተቋማት ላይ የከተማ ግብርና ስራ ቀጣይነት ባለው መንገድ እየተከናወነ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡ ይህ በየተቋማቱ የተጀመረው አበረታች ተግባር፤ ዜጎች በተመጣጣኝ ዋጋ የግብርና ምርቶችን እንዲሸምቱ ከማድረጉ ባለፈ፣ የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ በምግብ ራስን ለመቻል የሚደረገውን ብሔራዊ ግብ ከዳር ለማድረስ አበርክቶው የጎላ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በወልድያ ከተማ የተመዘገበው የልማት ውጤት ለዕድገት መሰረት የሚሆን ነው
Jun 12, 2026 1198
ወልድያ፤ ሰኔ 5/2018(ኢዜአ)፦ በወልድያ ከተማ የተመለከትነው የልማት ውጤት በችግር ውስጥም ሆኖ ህዝብን የሚጠቅምና ለእድገት መሰረት የሚሆን ስኬት ማስመዝገብ እንደሚቻል ተሞክሮ ያገኘንበት ነው ሲሉ በአማራ ክልል የተለያዩ ከተሞች ከንቲባዎች ገለጹ። የአማራ ክልል የ40 ከተሞች አስተዳደር ከንቲባዎችና የከተማና መሰረት ልማት ስራ አስኪያጆች በወልድያ ከተማ የተገነቡ የልማት ስራዎችን ማምሻውን ጎብኝተዋል። የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ተሾመ ዋለ በጉብኝቱ ወቅት እንደገለፁት፣ የተከናወነው ልማት ለወልድያ ከተማ አዲስ ፋና የፈነጠቀ ነው።   በጉብኝታችን የኮሪደር፣ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እና ሌሎች የልማት ስራዎች በአጭር ጊዜና በጥራት ተጠናቅቀው ለአገልግሎት የበቁ መሆናቸውን ተገንዝበናል ብለዋል። ይህም የአመራር ቁርጠኝነቱ ካለ በችግር ውስጥም ተሁኖ አስደማሚ የልማት ስራዎችን በማከናወን ህዝብን ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚቻል ማረጋገጫ መሆኑን ገልጸዋል። የከሚሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሸሪፍ ቃሲም በበኩላቸው የወልድያ ከተማ በፍጥነት ተለውጣ መመልከቴ ግርምትን ፈጥሮብኛል ብለዋል። የኮሪደር ልማቱና ሌሎች መሰረተ ልማቶች የከተማውን ገጽታ በመቀየር አዲስ ውበት ከማጎናጸፋቸው ባለፈ ትልቅ ልምድ የምንቀስምበት ነው ሲሉ ተናግረዋል።   አመራሩ ከህብረተሰቡ ጋር ተቀናጅቶ የሰራው ልማት የወልዲያ ከተማን ገጽታ በመቀየር አመርቂ ውጤት አስገኝቷል ያሉት ደግሞ የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ በድሉ ውብሸት ናቸው። የልማት ስራዎቹ በጥራትና በፍጥነት የተገነቡ በመሆናቸው በችግር ውስጥም ሆኖ ውጤታማ ልማት ማከናወን እንደሚቻል ተምረንበታል ብለዋል። በጉብኝቱ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ(ዶ/ር) እንዲሁም ሌሎች የክልልና የከተማ አስተዳደር አመራሮች ተሳትፈዋል።
በዞኑ በመኸር ወቅት ከ264 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ይለማል
Jun 12, 2026 435
አፍጥር፣ ሰኔ 5/2018 (ኢዜአ):-በጉራጌ ዞን በተያዘው የመኸር ወቅት ከ264 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች እንደሚለማ የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የዞኑ የ2018/19 የምርት ዘመን የመኸር ወቅት የሰብል ልማት ንቅናቄ መድረክ ''የተቀናጀ ግብርና ለቤተሰብ ብልፅግና'' በሚል መሪ ሃሳብ በቸሃ ወረዳ ተካሂዷል፡፡   የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ በበኩላቸው በዚህ ወቅት እንዳሉት በዞኑ በመኸር እርሻ ከ264 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይለማል። ለመኸር እርሻ ከ100 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ እየቀረበ መሆኑን ጠቁመው፣ 56 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ በመጠባበቂያነት መያዙንም ተናግረዋል፡፡ በመኸር ወቅቱ ስንዴ፣ ጤፍ፣ ቦለቄ፣ የቢራ ገብስ እና ሌሎች ሰብሎች እንደሚለሙ ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅትም የእርሻ ስራ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡ እንደ አቶ አበራ ገለጻ በመኸሩ ከሚለማው አጠቃላይ መሬት ውስጥ 41ሺህ 800 ሄክታሩ በኩታ ገጠም የሚለማ ነው።   የቸሃ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ደሱ ድንቁ በበኩላቸው እንዳሉት በዓመት ከሦስት ጊዜ በላይ ለማምረት የሚያስችል አሰራር በመዘርጋቱ በግብርና ምርት ላይ ስኬቶች እየተመዘገቡ ነው። የምርት ማሳደጊያ ግብዓት በወቅቱ ከማሰራጨት ባለፈ የአርሶ አደሩን ፍላጎት እና አቅም በሚገባ በመለየት በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በተፋሰስ የለሙ አካባቢዎች ጭምር በተለያዩ ሰብሎች እየለሙ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጌታ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሙዘፋ የሱፍ ናቸው። የወረዳው አርሶ አደሮች በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ገቢ የሚያስገኙ ምርቶች ላይ እንዲያተኩሩ በመደረጉ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ህይወታቸውን እየቀየሩ መጥተዋል ብለዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የተገኙት የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ በዞኑ በሌማት ትሩፋት በተከናወኑ የዶሮ እርባታ፣ የወተት እና የእንስሳት ልማት ስራዎች እንዲሁም በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል።   በሰብል ልማትም ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ያሉት አስተዳዳሪው በተያዘው የመኸር እርሻ አንድም መሬት ጾም እንዳያድር ልማቱን ማጠናከር እንደሚገባ አሳስበዋል። በበልግ ወቅት በዝናብ ስርጭት መዘግየት ምክንያት የጠፋውን የበቆሎ ሰብልን ለማካካስ አስፈላጊው የግብርና ግብዓት በመጠቀምና የተሻሻሉ አሰራሮችን በመተግበር ይሰራል ሲሉም አክለዋል። በመድረኩ የተለያዩ ወረዳዎች እና ከተማ አመራሮች፣ የግብርና ባለሙያዎች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
የኢትዮጵያን የቡና ምርት ጥራትና ምርታማነት የሚያሻሽሉ የቴክኖሎጂ ግብዓቶች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ እየተደረጉ ነው
Jun 12, 2026 399
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያን የቡና ምርት ጥራትና ምርታማነት የሚያሻሽሉ የቴክኖሎጂ ግብዓቶች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑን የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ለቡና አምራች አርሶ አደሮች የሚውሉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ የግብርና ግብዓቶች አስረክቧል።   ለቡና አምራች አርሶ አደሮች የሚተላለፉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ የግብርና ግብዓቶችም የክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊዎች ከኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ተረክበዋል። የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ በግብርና መስክ የተመዘገበው ስኬት ለቡና ምርት ጥራትና ምርታማነት ወሳኝ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል። ባለስልጣኑ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን፣ የጥራት ቁጥጥር መሳሪያዎችንና ሌሎች ግብዓቶችን ለክልል በማከፋፈል ለአርሶ አደሩ ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በቡና ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች በቴክኖሎጂ የተደገፉ ግብዓቶች በማቅረብ ጥራቱ የጠበቀ ምርት እንዲያመርቱ በማስቻል የተሻለ ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል። ግብዓቶቹ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የቀረቡ ሲሆን ቡና አብቃይ በሆኑ ክልሎች የተመረጡ ወረዳዎች ለሞዴል አርሶ አደሮች ተደራሽ እንደሚሆኑ ገልፀዋል። ከዓመታት በፊት በሔክታር 6 ኩንታል ሲመረት የነበረ መሬት አሁን ላይ በሔክታር ከአስር ኩንታል በላይ ቡና ማምረት እየተቻለ መሆኑን አንስተዋል። በዛሬው እለትም 62 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመቱ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የሚጠቀሙ የግብርና ግብዓቶች ለቡና አምራች አርሶ አደሮች መተላለፋቸውን አረጋግጠዋል። ግብዓቶቹ የቡና ምርታማነትንና ጥራትን በማሳደግ አርሶ አደሮችን ከዘመናዊ ቴክኖሎጂ ተጠቃሚነት ጋር እንደሚያላምዱ ጠቅሰዋል። ቴክኖሎጂዎቹም የቡና ምርታማነት ተወዳዳሪነትን በማሳደግ ዓለም አፍ የገበያ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ እንደሚያግዙ አስረድተዋል። የተሻለ ምርትና ምርታማነት በማረጋገጥ ምርቱ ጥራቱ ጠብቆ በዓለም ገበያ ላይ ተወዳዳሪነትን የሚያሳድጉ ሰፋፊ ስራዎች መከናወናቸውን አንስተዋል። በርክክቡ የተገኙት ኦሮሚያ ክልል ቡናና ሻይ ልማት ዳይሬክተር ታከለ ሃይለማርያም፤የክልሉ መንግስት የቡና ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የተሰጡት ግብዓቶችም የበዘርፉ የተሰማሩ እርሶ አደሮች ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ትልቅ አስተዋፅኦ የሚያበረክቱ በመሆናቸው አርሶ አደሩ በአግባቡ የሚጠቀምበት ይሆናል ብለዋል። የሲዳማ ክልልን ወክለው የመጡት ቡዙነህ ቡናዬ በበኩላቸው፤ ባለስልጣኑ ልዩ ልዩ ዘመናዊ የግብርና ግብአቶች ሲያቀርብ መቆየቱንና በዚህም የተሻለ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ከአፍሪካ ሰማይ እስከ ዓለም ከፍታ፡የኢትዮጵያ አየር መንገድ ያልተቋረጠ የስኬት ጉዞ!
Jun 12, 2026 2008
በኢዜአ ዐይን ...! በዮሐንስ ደርበው የኢትዮጵያ የዘመናት ስኬት መገለጫ፤የአፍሪካ አቪዬሽን ማዕከል እና በኢንዱስትሪው በዓለም ስመጥር ተቋማት መካከል አንዱ ነው ! የኢትዮጵያ አየር መንገድ። አየር መንገዱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ በማስገባት፣ የሥራ ዕድል በመፍጠር፣ የኢትዮጵያን ወጪ ንግድ በመደገፍ፣ኢትዮጵያን በአቪዬሽን መሠረተ-ልማት ከፍ በማድረግ፣የቱሪዝም ዘርፉን በማገዝ እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ አፍተኛ አስተዋጽዖ እያበረከተ ነው። አየር መንገዱ ወደ ካይሮ "አንድ" ብሎ የጀመረው ታሪካዊ ጉዞ ዛሬ ላይ በአምስት አኅጉራት 145 መዳረሻዎችና በ147 ዘመናዊ አውሮፕላኖች አገልግሎቱን እያቀላጠፈም ይገኛል። አየር መንገድ የገነባው ዐቅም በዓለም መድረክ ላይ ተወዳዳሪ እንዲሆን ያስቻሉት ሲሆን የወደፊት ዕቅድና የዐቅም ግንባታ ትኩረቶቹ ለቀጣይ ስኬቱ ቁልፍ እንደሚሆኑም ይጠበቃል። በተለያዩ ጊዜያትም ዓለም አቀፍ፣አኅጉር አቀፍ እና ሀገር አቀፍ ሽልማቶችን መሰብሰቡ ለዚህ ሁነኛ አስረጂ ይሆናል።የበረራ አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት፤የተቋማዊ ዕድገቱን ማስቀጠል እንዳስቻለውም ይገለጻል። አየር መንገዱ በታላቅነቱ ተፎካካሪ ሆኖ ለመዝለቅ የሀገር ውስጥ አቅሙን ማሳደግ እና የነበሩ አውሮፕላን ማረፊያዎችን በማደስ፣በማስፋፋት፣በማዘመን፣አዳዲስ በመገንባት ክልሎችን በአየር ትራንስፖርት በማስተሳሰር ለዜጎቹ ምቹ ሁኔታ እንዲኖር በልዩ ትኩረት እየሠራ ይገኛል። በሌሎች ዘርፎች የተመዘገቡትን ስኬቶች በቴክኖሎጂውም ለልብ ህመም አጋላጭ መንስዔዎች ምንድን ናቸው? የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የሀገር ውስጥ መዳረሻውን በቅርቡ አስመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ማድረጉም የእዚሁ ትጋት አንዱ ማሳያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል።ይህ መዳረሻ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ ነው። ይህ መሠረተ-ልማትም ለአካባቢው ነዋሪ፣ የንግዱ ማኅበረሰብ እና ቱሪዝም ትልቅ ሥጦታ ነው። የምንገነባው እያንዳንዱ አዲስ የአውሮፕላን ማረፊያ ርቀትን በማጥበብ ትስስር ይፈጥራል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ይህም የክልሎችን ኢኮኖሚያዊ ዐቅም ያነቃቃል እንዲሁም ሕዝባችንን ይበልጥ ያቀራርባል ብለዋል። ‎ የአፍሪካ ኩራት የሆነውና 80ኛ ዓመቱን የያዘው አየር መንገዱ በእርግጥም “የአፍሪካ አዲሱ መንፈስ” (The New Spirit of Africa!”) ነው ሲሉ ገልጸውታል። በዚህም የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአዳዲስ የመንገደኛ አውሮፕላን፣ የበረራ መዳረሻ በማስፋትና በሀገር ውስጥ የአውሮፕላን ማረፊያ መሠረተ-ልማት ግንባታ አስደናቂ ሥራ እየሠራ ነው። በሰፊ የአውታረ መረብ መስመሮች በርካታ ሀገራትን ተደራሽ በማድረግ ግንባር ቀደም ከሚባሉት ጥቂት አየር መንገዶች አንዱ ለመሆንም በቅቷል። አየር መንገዱ መንገደኞችን ከሀገር ሀገር ከማዘዋወር፤ከፍተኛ የካርጎ አገልግሎትን ከማቀላጠፍ ባሻገርም በሀገራት መካከል ንግድን፣ቱሪዝምን፣ኢንቨስትመንትን እና ውህደትን በመፍጠር በኩል ለአመታት የዘለቀ ዝናን አትርፏል። ይህ የተለያዩ አውሮፕላን ማረፊያዎችን የመገንባት ስትራቴጂ ኢትዮጵያን የወደፊቷ የአፍሪካ ግንባር ቀደም የአየር ትራንስፖርት በር የማድረግ ዓላማን ያነገበ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታን ባስጀመሩበት ወቅትም የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በአፍሪካ ታሪክ ትልቁ የአየር ትራንስፖርት መሠረተ-ልማት ፕሮጀክት እንደሚሆን መግለጻቸው ይታወሳል። ይህም የኢትዮጵያን ፈጣን የአየር ትራንስፖርት እድገት እና እየሰፋ የመጣውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዓለም አቀፍ ትስስር ዘላቂ በማድረግ ከቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በተጨማሪ አዲስ ሜጋፕሮጀክት እየለማ ይገኛል ማለታቸው የዚሁ ማሳያ ነው። #በኢዜአ_ዐይን…! #ኢዜአ #የኢትዮጵያ_አየር_መንገድ #Ethiopian_News_Agency
በብሔረሰብ አስተዳደሩ ለአርሶ አደሩ የብድር አገልግሎት በማቅረብ ተጠቃሚነቱን የማሳደግ ተግባር እየተከናወነ ነው
Jun 12, 2026 165
ሰቆጣ፤ሰኔ 5/2018 (ኢዜአ)፡- በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ለአርሶ አደሩ የብድር አገልግሎት በማቅረብ ተጠቃሚ የሚሆንበት አሰራር ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑ ተገለጸ። በመምሪያው የመሬት አስተዳደር ባለሙያ አቶ ቤተማርያም ሸጋው ለኢዜአ እንደገለፁት በብሔረሰብ አስተዳደሩ ለ330 ሺህ አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር ተሰጥቷል። ይህም አርሶ አደሩ ደብተሩን በማስያዣነት ተጠቅሞ ገንዘብ በመበደር ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም 624 አርሶ አደሮች በይዞታ ማረጋገጫ ደብተራቸው አማካኝነት የብድር አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ብድሩ መመቻቸቱም አርሶ አደሩ ከሰብል ልማቱ በተጨማሪ በእንስሳት ማድለብ፣ በወተት፣ በንብ ማነብና በሌሎች የገቢ ማስገኛ የልማት ስራዎች እንዲሳተፉ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አስረድተዋል። ይህም የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባሻገር ተጨማሪ ሃብት ለማፍራት የሚያስችል መሆኑንም አክለዋል። በጋዝጊብላ ወረዳ የ01 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ዋጋው ካሴ እንደገለጹት ግማሽ ሄክታር የእርሻ ማሳቸውን በማስያዝ የ99 ሺህ ብር ብድር ተጠቃሚ መሆናቸውን አስረድተዋል። በይዞታ ማረጋገጫ ደብተር የብድር አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸው ለልማት እንዲተጉ እንደሚያደርጋቸው ጠቁመው በተበደሩት ገንዘብም በከብት ማድለብ ስራ መሰማራታቸውን ተናግረዋል። ሌላዋ የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ራሄል ክንፈ በበኩላቸው ብድሩ መመቻቸቱ ከሰብል ልማት ባለፈ በከብት ማድለብና በሌሎች የስራ መስኮች ለመሰማራት እንዳስቻላቸው ገልጸዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን ከ50 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የስራ እድል ተፈጥሯል
Jun 12, 2026 182
ነገሌ ቦረና፤ ሰኔ 5 /2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ቦረና ዞን በበጀት አመቱ እስካሁን ከ50 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የስራ እድል መፈጠሩን የዞኑ የስራ እድል ፈጠራና ክህሎት ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የእቅድና በጀት ክትትል ቡድን መሪ አቶ ሊበን ሀላኬ፣ በበጀት አመቱ ለ53 ሺህ 26 ወጣቶች የስራ እድል ለማመቻቸት ታቅዶ ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል፡፡ ነገሌ ቦረና ከተማ አስተዳደርን ጨምሮ በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች በበጀት ዓመቱ እስካሁን 51 ሺህ 669 ወጣቶች የስራ እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። ወጣቶቹ ከተሰማሩበት የስራ መስኮች መካከል በግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ንግድና ማህበራዊ አገልግሎት ዘርፎች ዋና ዋናዎቹ እንደሆኑ አመልክተዋል፡፡ ወጣቶቹ ወደ ስራ የገቡት በ2 ሺህ 258 ህብረት ስራ ማህበራት በመደራጀት መሆኑን ጠቁመው፣ ወደ ስራ ከገቡት መካከል 23 ሺህ 189 ሴቶችና የከፍተኛ ትምህርት ምሩቃን ወጣቶች ይገኙበታል ብለዋል። የስራ እድል ተጠቃሚ ለሆኑ ወጣቶች የብድር አገልግሎት መመቻቸቱንም አክለዋል። ለስራ እድል ተጠቃሚዎቹ በገጠር 458 ሄክታር የማምረቻ ቦታና በከተሞች ደግሞ 38 የመሸጫ ሼዶች መቅረባቸውን ተናግረዋል።   የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪ ወጣት ኤልያስ ቀንአ፣ በልብስ ስፌት ስራ በመሰማራት የተለያዩ አልባሳትን በማዘጋጀት እንደሚተዳደር ተናግሯል። በመንግስት የተመቻቸው የማምረቻ፣ የመሸጫ ቦታና የብድር አቅርቦት ለስራችን ስኬት እገዛ እያደረገልን ነው ብሏል ወጣቱ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም