ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሞሪሺየስ የጀመረው አዲስ ቀጥታ በረራ ለንግድ፣ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት አዳዲስ ዕድሎችን ይፈጥራል
Jul 11, 2026 823
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሞሪሺየስ የጀመረው አዲስ ቀጥታ በረራ ለንግድ፣ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት አዳዲስ ዕድሎችን እንደሚፈጥር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሃደራ አበራ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሞሪሺየስ ዋና ከተማ ፖርት ሉዊስ የቀጥታ በረራ መጀመሩን ይፋ አድርጓል፡፡ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሞሪሺየስ የጀመረው አዲስ ቀጥታ በረራ የአፍሪካን ተደራሽነት በማስፋት የትስስር ጥረቱን የሚያጠናክር ስኬታማ ምዕራፍ ነው ተብሏል፡፡ የበረራው ማስጀመሪያ የመርሐግብር ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሃደራ አበራ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው፣ በኢትዮጵያ የሞሪሺየስ ሪፐብሊክ አምባሳደር ኢንድራርጂት ባምቦዋ እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በመርሐግብሩ ንግግር ያደረጉት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሃደራ አበራ እንዳሉት፣ አዲሱ የበረራ አገልግሎት የሁለቱ ሀገራት የአፍሪካ ውህደትን ለማጠናከር ያላቸውን ቁርጠኝነት ያሳያል። ይህ ድልድይ ለቀጠናዊ ትስስር፣ ለንግድ፣ ለቱሪዝም፣ ለኢንቨስትመንትና ለባሕል ልውውጥ አዳዲስ ዕድሎችን እንደሚፈጥር ገልጸዋል። በሞሪሺየስ እና በአዲስ አበባ በኩል ወደ ቀሪው ዓለም የሚደረገውን ጉዞ በማቀላጠፍ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቱን እንደሚያጠናክሩ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው በበኩላቸው፣ አዲሱ መስመር አየር መንገዱ በአፍሪካ ያለውን ትስስር ለማሳደግ ያለውን ስትራቴጂያዊ እቅድ ያሳያል ብለዋል። ሞሪሺየስ የአየር መንገዱ 41ኛዋ የአፍሪካ መዳረሻ መሆኗን የጠቆሙት ዋና ስራ አስፈጻሚው፣ ይህ በረራ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠና (AfCFTA) ዓላማዎችን በመደገፍ የኢኮኖሚ ትብብርን እንደሚያሻሽል አስረድተዋል። በኢትዮጵያ የሞሪሺየስ አምባሳደር ኢንደራርጂት ባምቡዋ፣ ይህ የበረራ መጀመር በሁለትዮሽ ግንኙነት ውስጥ የአዲስ ምዕራፍ መጀመሪያ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድን የአፍሪካ ልቀት፣ ጽናትና ፈጠራ ምልክት ሲሉ ያደነቁ ሲሆን፣ አዲሱ መስመር በአፍሪካ እና በሕንድ ውቅያኖስ ቀጠና መካከል ያለውን ትስስር በእጅጉ እንደሚያሳድግም እምነታቸውን ገልጸዋል። ይህ አዲስ የበረራ አገልግሎት የኢትዮጵያ አየር መንገድ አፍሪካን ከዓለም ጋር የሚያገናኝበትን መረብ ይበልጥ ያጠናክራል።
በአዲስ አበባ የተገነቡ የመንገድ መሠረተ ልማቶች ለትራፊክ ፍሰቱ መሳለጥ አዎንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው
Jul 11, 2026 500
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ የተገነቡ የመንገድ መሠረተ ልማቶችና የኮሪደር ልማት ሥራዎች ለትራፊክ ፍሰቱ መሳለጥ አዎንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙ አስተያየታቸውን የሰጡ አሽከርካሪዎች ገለጹ። የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ በማዘመን እና ዘመናዊ የመንገድ መሰረተ-ልማቶችን በመዘርጋት፣ የትራፊክ ፍሰትን ከማቀላጠፍ ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹ፣ ደህንነቱ የተጠበቀና ቀልጣፋ አካባቢን መፍጠር አስችሏል፡፡ ሰፊና ደረጃቸውን የጠበቁ የእግረኛ መንገዶች በመገንባታቸው የከተማዋን ነዋሪዎች ሰላማዊ እንቅስቃሴ ከማረጋገጡም በላይ፣ የመንገድ ተጠቃሚዎችን ደህንነት በማስጠበቅ የትራፊክ አደጋዎችን ለመቀነስ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። አስተያየታቸውን የሰጡ አሽከርካሪዎች በከተማዋ የተሰሩት አዳዲስ መንገዶች እና የኮሪደር ልማት ስራዎች የትራፊክ ፍሰቱን በማሳለጥ አዎንታዊ ለውጥ አምጥተዋል ብለዋል።   አሽከርካሪ የሆኑት ኃይሌ ዘመድኩን እና ጤናዬ ጠንክር እንደገለጹት፤ የኮሪደር ልማቱ ለትራፊክ ፍሰት አመቺ እና ዘመናዊ መንገዶችን በመፍጠር ስጋት የለሽ የማሽከርከር ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል። የከተማዋን ገጽታ በእጅጉ የቀየሩት እነዚህ ውብና ሰፋፊ መንገዶች፣ የዲዛይን ጥራታቸውና የተሟላ የመንገድ ምልክቶቻቸው ለትራፊክ አደጋ መቀነስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛሉ ብለዋል።   የኮሪደር ልማት ለከተማዋ ውበት ብቻ ሳይሆን፣ ለአሽከርካሪዎች የላቀ የደህንነት ስሜትና የጉዞ ቅልጥፍናን የሰጠ ስኬታማ የልማት ስራ መሆኑን ጠቅሰዋል። አሽከርካሪ ብሩክ ግሩም፤ የኮሪደር ልማቱ የነበረውን ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ በመቅረፍ ተሽከርካሪዎች በነጻነት እንዲንቀሳቀሱ በማድረጉ ጉዞን በአጭርና በአስተማማኝ ሁኔታ ማከናወን ተችሏል ብለዋል።   የመንገድ አቅም መጨመሩ ለትራፊክ ፍሰቱ መሻሻል ብቻ ሳይሆን፣ አደጋዎችን በእጅጉ በመቀነስ ለአሽከርካሪዎች ትልቅ የደህንነት እፎይታን የፈጠረ ውጤታማ የልማት ስራ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የአዲስ አበባ ትራፊክ ማኔጅመንት ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ኤልያስ ዘርጋ እንደገለጹት፤ የተከናወኑት የኮሪደር ልማት ስራዎች የትራፊክ ፍሰቱን በማቀላጠፍና የከተማዋን የትራንስፖርት እንቅስቃሴ ሰላማዊ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ነው።   ይህ ዘመናዊ የመንገድ አውታር እግረኞች በደህንነት ተጠብቀው በፍጥነት እንዲንቀሳቀሱ ምቹ ሁኔታን በመፍጠሩ፣ በያዝነው በጀት ዓመት በሰውና በንብረት ላይ ይደርስ የነበረውን የመንገድ አደጋ በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ ተችሏል ብለዋል። ፕሮጀክቱ የመንገድ ደህንነትን በማረጋገጥና የትራፊክ መጨናነቅን በማስወገድ፣ በከተማዋ ለሚደረግ ማንኛውም አይነት የጉዞ እንቅስቃሴ አስተማማኝና ቀልጣፋ አማራጭ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በዞኑ የተገኘው ሰላም የግብርና ስራችንን በተረጋጋና በተደራጀ መልኩ ለማከናወን አስችሎናል - አርሶ አደሮች
Jul 11, 2026 424
ገንዳውኃ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ምዕራብ ጎንደር ዞን የተገኘው ሰላም የግብርና ስራቸውን በተረጋጋና በተደራጀ መልኩ ማከናወን እንዳስቻላቸው አርሶ አደሮች ተናገሩ። አርሶ አደር ሱሌማን ዳውድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአካባቢያችን ሰላም ለማስጠበቅ ባደረግናቸው ጥረቶች የእርሻ ስራችን በተገቢው መንገድ ለማከናወን አስችሎናል። በአሁኑ ወቅትም በ10 ሄክታር መሬታቸውን በሰሊጥ፣ በአኩሪ አተርና ሌሎች ሰብሎች ለመሸፈን የዘር ስራ መጀመራቸውን ነው የገለጹት። አርሶ አደር ደጀኔ አሰፋ በበኩላቸው፣ ዞኑ ለግብርና ልማት ያለው ፀጋ ለወጭ ንግድ የሚሆኑ ምርቶችን በስፋት ለማምረት እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። በዘንድሮው ክረምትም ባለኝ 20 ሔክታር መሬት ላይ ጥጥ፣ ሰሊጥ፣ አኩሪ አተርና ሌሎች ሰብሎችን በመዝራት እስከ 200 ኩንታል ምርት ለማግኘት እየሰራሁ ነው ብለዋል። በአካባቢው የተፈጠረው ሰላም አርሶ አደሩ፣ ባለሃብቱና የጉልበት ሰራተኛው ተረጋግቶ እንዲሰራ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የገለጹት ደግሞ በእርሻ ኢንቨስትመንት የተሰማሩት አቶ ቃሲም እንድሪስ ናቸው። ያላቸውን 65 ሄክታር መሬት በዘመናዊ መንገድ በማልማት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። የምዕራብ ጎንደር ዞን አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አንዳርጌ ጌጡ እንደገለጹት፤ ማሕበረሰቡ የአካባቢውን ሰላም ለማረጋገጥ ከአመራሩ እና ከጸጥታ ኃይሉ ጋር በቅንጅት እየሰራ ይገኛል። በዚህም አስተማማኝ ሰላም እየተፈጠረ በመምጣቱ በዘመናዊ ትራክተሮችና ሜካናይዜሽን ታግዞ የግብርና ስራን ለማቀላጠፍ እንተቻለ ነው የተናገሩት። በተገኘው ሰላም ለአርሶ አደሩና ባለሃብቱ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶችና የምርት ማሳደጊያ ግብዓትን በወቅቱ ለማቅረብም እንደተቻለ ነው ያመለከቱት። በዘንድሮው የመኸር እርሻ 529 ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ የተገባ ሲሆን በአሁኑ ወቅትም ከ450 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ በዘር ተሽፍኗል ብለዋል። የዞኑ ህብረተሰብም ሰላም የሁሉም መሰረት መሆኑን በመገንዘብ ከጸጥታ አካላት ጎን በመሰለፍ ያረጋገጠውን ሰላም አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው አስገንዝበዋል።
በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ከ60 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Jul 11, 2026 278
ደሴ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን በመኸር እርሻ ከ60 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ ተገኝ አባተ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል የሚያግዙ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በዚህም በመኸር እርሻ 231 ሺህ 566 ሄክታር መሬት በማልማት ከሰባት ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን ገልጸዋል። የዝናቡ ወቅት ቀድሞ በጀመረባቸው አካባቢዎች እስካሁን ከ60 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን ማሳ በዘር መሸፈኑንም ነው ያመለከቱት። አርሶ አደሩ የተሻሻሉ አሰራሮችንና ቴክኖሎጅዎችን እንዲጠቀም በማድረግ ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ ከ160 ሺህ ኩንታል በላይ ዘመናዊ ማዳበሪያ መሰራጨቱን ነው የገለጹት። የዝናብ መዘግየት ባለባቸው አካባቢዎች ደግሞ የመስኖ አማራጭን በመጠቀም የመኸር ሰብል ልማቱን እንዲያከናውኑ ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በሰሜን ወሎ ዞን ባለፈው የመኸር ምርት ዘመን ከለማው 231ሺህ ሄክታር መሬት አምስት ነጥብ ስምንት ሚሊየን ኩንታል ምርት መገኘቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በወጪ ንግድ የተመዘገበውን ውጤት ይበልጥ ለማሳደግ በምርት ጥራትና እሴት መጨመር ላይ ትኩረት ተደርጓል - ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)
Jul 11, 2026 146
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ):- በሀገሪቱ በወጪ ንግድ የተመዘገበውን ውጤት ይበልጥ ለማሳደግ በምርት ጥራትና እሴት መጨመር ላይ በትኩረት እንደሚሰራ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስትሩ የይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክን የሥራ እንቅስቃሴ የጎበኙ ሲሆን፣ በፓርኩ የአቮካዶ፣ ዘይትና ቡናን የሚያቀናብሩ ኩባንያዎችን ተመልክተዋል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደተናገሩት፤ መንግሥት የወጪ ንግድ ገቢን ለማሳደግ በእሴት መጨመር ሥራ ላይ የሚደረጉ ጥረቶችን ለማጠናከር ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ይገኛል። በተለይም በግብርናው ዘርፍ ያለውን አቅም በአግባቡ በመጠቀምና ገበያው በሚፈልገው መልኩ እሴት ጨምሮ መላክ ላይ የተጀመሩ ጥረቶች የሚጠናከሩ ናቸው ብለዋል። በፓርኩም በአቮካዶና በቡና ዘርፍ በመሰማራት እሴት በመጨመር የወጪ ገቢ ግኝትና ተኪ ምርት ላይ የተሰማሩ ኩባንያዎችን መመልከታቸውን ጠቅሰው፤ ተግባሩን አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በዘንድሮ ዓመት ከወጪ ንግድ ከ11 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ በማግኘት ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ መቻሏን ያወሱት ሚኒስትሩ፤ በፓርኩ የሚታዩ እንቅስቃሴዎችን ማሳደግ ይገባልም ብለዋል። በእስካሁኑ ሂደትም ተኪ ምርቶች ላይ እንደሀገር እየተገኘ ያለውን ውጤት ለማጠናከር የሚደረጉ ጥረቶች አበረታች መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። በዚህ ሂደት ደግሞ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ፓርኮች መቋቋማቸው ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በኢንዱስትሪ ፓርኩ ቡናን በማቀነባበር ስራ ላይ የተሰማራው የ“መይ መይ ቡና ፕሮሰሲንግ” ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ሥራ አስኪያጅ ሚስተር ጄይ ሰን፣ በመንግሥት በተደረገላቸው ድጋፍ ታግዘው ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቅሰዋል።
በክልሉ በመንግሥትና በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ቅንጅት ማኅበረሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jul 11, 2026 103
አርባ ምንጭ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በመንግሥትና በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ቅንጅት በተሠራው ሥራ ማኅበረሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ተግባራት መከናወናቸውን የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ አስታወቀ። ክልል አቀፍ የመንግሥትና የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የጋራ ምክክር ፎረም በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ተፈሪ አባተ በመድረኩ ባስተላለፉት መልዕክት፤ የክልሉን ሀብት በአግባቡ በማስተዳደር፣ የዜጎችን የልማት ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንዲሁም መሠረታዊ የኢኮኖሚ ለውጥ ለማምጣት በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። መንግሥት ለቀረጻቸው ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ስኬት፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች በኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ልማት ግንባታ ውስጥ ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑን አብራርተዋል። ለዚህም ድርጅቶቹ በተለይ በውኃ፣ በሳኒቴሽንና ሃይጂን፤ በጤና እና በግብርና፣ በኑሮ ማሻሻያ እና በትምህርት እንዲሁም በአካባቢ ጥበቃ እንዲሁም በሌሎች ማኅበራዊ ዘርፎች ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን በማሳያነት ጠቅሰዋል። በቀጣይም መሠረታዊ አገልግሎቶችን ለሕብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ቅንጅታዊ አሠራሮች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።   የቢሮው ምክትልና የፊሲካል ፖሊሲ ትብብር ዘርፍ ኃላፊ ታምራት ታንጋ በበኩላቸው፤ የምክክር መድረኩ ዋና ዓላማ በመንግሥትና በሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች መካከል ያለውን አጋርነትና ትብብር ለማጠናከር ነው ብለዋል። የሁለቱ አካላት ጥምረት የሕዝቡን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት የሚያሳድግ በመሆኑ በመካከላቸው ያለው ጥብቅ ትብብር ለክልሉ ዕድገትና ልማት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል።   የክልሉ ሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ማስተባበሪያ ዋና ዳይሬክተር ማሞ ሙልሶ፣ የክልሉን ማኅበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ አረጋግጠዋል።
በአማራ ክልል በማዕድን ዘርፍ በተከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጨባጭ ለውጥ ማስመዝገብ ተችሏል
Jul 11, 2026 86
ባህር ዳር ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የማዕድን ሃብትን በጥናት በመለየት በተካሄደ የማልማት ተግባር ተጨባጭ ለውጥ መመዝገቡን የክልሉ ማዕድን ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የማዕድን ዘርፉ ተኪ ምርትና የውጭ ምንዛሬን ከማስገኘት ባለፈ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ አይተኬ ኢኮኖሚያዊ ሚናውን እየተወጣ ይገኛል። በቢሮው የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ዝናው አበበ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በክልሉ የሚገኘውን የማዕድን ሀብት በጥናትና ምርምር በመለየት ወደ ልማት እንዲገባ እየተደረገ ይገኛል። በተለይም ባለፉት የለውጥ ዓመታት የማዕድን ዘርፉ በክልሉ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ውስጥ ሚናውን እንዲወጣ ለማድረግ የተሰራው ሥራ ተጨባጭ ለውጥ ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲዎችን በማሳተፍ የተፈጥሮ ጸጋን ለመለየት በተደረገው ሳይንሳዊ ጥናት በርካታ የማዕድን ሀብት በዓይነትም ሆነ በብዛት መኖሩ ተረጋግጧል ብለዋል። በተለይም የወርቅና የግራናይት ማዕድናትን ጨምሮ የድንጋይ ከሰል፣ ኦፓል፣ ብረትና መሰል ማዕድናት በበቂ መጠን እንዳሉ በማረጋገጥ ወደ ልማት እንዲገቡ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የማዕድን ዘርፉ ኢኮኖሚውን ከማነቃቃት ባሻገር፣ ከ73 ሺህ ለሚበልጡ ወገኖች የሥራ ዕድል በመፍጠር በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለም አብራርተዋል። ዘርፉን የበለጠ አጠናክሮ ለማስቀጠልም ለ198 ባለሀብቶች አዳዲስ የምርመራና የምርት ፈቃዶች ተሰጥተዋል። እንዲሁም ለ2 ሺህ 835 ኢንተርፕራይዞች የባህላዊ እና ለ354 አነስተኛ የኮንስትራክሽን ድርጅቶች የማምረቻ ፈቃድ በመስጠት ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉንም ጠቁመዋል። በማዕድን ዘርፉ የተገኙ ተጨባጭ ውጤቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠልም የ25 ዓመት የልማትና የ5 ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ወደ ትግበራ መግባቱን አክለው ገልጸዋል።
በክልሉ የግብርና ሥራን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው
Jul 11, 2026 143
ወላይታ ሶዶ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና ሥራን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢዎች ልማት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በወላይታ ዞን ዱጉና ፋንጎ ወረዳ ከ21 ሚሊዮን 500 ሺህ ብር በላይ በሆነ ወጪ ያስገነባውን የብላቴ ኤታ መስኖ አውታር ለአገልግሎት አብቅቷል።   በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የቢሮው ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር እንደገለጹት፤ በክልሉ የመስኖ አውታሮችን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሠራ ይገኛል። ይህም አርሶ አደሩን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ በዓመት ሁለትና ሦስት ጊዜ በማምረት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ ይገኛል ብለዋል።   ዛሬ የተመረቀው ፕሮጀክትም ከ1 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት የማልማት አቅም ያለው ሲሆን፤ ከ1 ሺህ 200 በላይ አርሶ አደሮችን ቀጥተኛ ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ኃላፊው አብራርተዋል። የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ በበኩላቸው፤ በዞኑ የሚገኙ አርሶ አደሮች ያሉትን የውኃ አማራጮች በመጠቀም በመስኖ እንዲያለሙ በተደረገው ጥረት ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል።   ሥራው አርሶ አደሩን ከተረጂነት በማላቀቅ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ ትልቅ አቅም መፍጠሩን ጠቅሰዋል፡፡ የዱጉና ፋንጎ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘካሪያስ ዎንታሞ በበኩላቸው፤ በወረዳው ሰፊ ሊለማ የሚችል የእርሻ መሬት መኖሩን ጠቅሰው፣ አርሶ አደሮች በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ በማልማት ወደተሻለ የኑሮ ደረጃ እየተሸጋገሩ መሆኑን ተናግረዋል።   ዛሬ የተመረቀው የመስኖ ፕሮጀክትም የሦስት ቀበሌ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የብላቴ ኤታ እና የፓንጎ ቢጆ ቀበሌ አርሶ አደሮች፤ ቀደም ሲል የዝናብ ወቅትን ብቻ በመጠበቅ በዓመት አንድ ጊዜ ያመርቱ እንደነበርና ኑሯቸውም ከእጅ ወደ አፍ እንደነበር አስታውሰዋል። ከዚህ በኋላ በመስኖው በመታገዝ ሰብል እንዲሁም አትክልትና ፍራፍሬዎችን በማምረት ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተናግረዋል።
በምዕራብ እና ምስራቅ ሐረርጌ ዞኖች የሚገኙ ፓርኮችን የቱሪዝም መዳረሻነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው
Jul 11, 2026 134
፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብና ምስራቅ ሐረርጌ ዞኖች የሚገኙ ሦስት ፓርኮችን በማልማትና በማስተዋወቅ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸውን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ደንና ዱር እንስሳት ድርጅት አስታወቀ። የኦሮሚያ ክልል ደንና ዱር እንስሳት ድርጅት የሐረርጌ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ ፋኪያ ጀማል ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ ከተቋቋሙት አዳዲስ ፓርኮች ሁለቱ በምዕራብ ሐረርጌ ዞን፣ አንዱ ደግሞ በምስራቅ ሐረርጌ የሚገኝ ነው።   በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ገመቺስ እና አንጫር ወረዳዎች የተቋቋሙት የባሬሞ እና የድንድን ፓርኮች የደን ይዘት እና የዱር እንስሳት መጠን ለማሳደግ የተፈጥሮ ዛፍ ችግኞችን በብዛት የመትከል፣ ደኑን የመጠበቅና የመንከባከብ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን አመልክተዋል። በዚህ ወቅትም የፓርኮቹ የደን መጠን እያደገ በመምጣቱም እንደ አጋዘን፣ ከርከሮ፣ ድኩላ፣ ጉሬዛና ሌሎች የዱር እንስሳት ቁጥር እየጨመረ መምጣቱንም ተናግረዋል። በደኖቹ ውስጥ ከሚገኙ እንደ አጋዘን ካሉ እንስሳት ሕጋዊ አደን ገቢ እየተገኘ መሆኑን ገልጸው፣ ከዚህም የአካባቢው አርሶ አደሮች ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። በዚህ ዓመት ከእንስሳት አደን ከተገኘው ገቢ ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆነው በደን እንክብካቤ ለተሰማሩ የአካባቢው አርሶ አደሮች መሰጠቱን አብራርተዋል። በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ኩርፋ ጨሌ ወረዳ የተቋቋመው የደባል ሞቲ ጋራ ፓርክ በታሪካዊ ስፍራነቱና በተራራማ አቀማመጡ ለቱሪዝም ልማት ለማዋል የማስተዋወቅ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በጽሕፈት ቤቱ የፓርኮች እና ኢኮ ቱሪዝም ባለሙያ አቶ ጀቤሳ ፊጡማ በበኩላቸው፣ በምስራቅ ሐረርጌ ዞን የኩርፋ ጨሌ፣ ቀርሳ፣ ገረዋ እና በደኖ ወረዳዎችን የሚያዋስነው የደባል ሞቲ ጋራ ፓርክን በስፋት በማስተዋወቅና በማልማት የቱሪዝም መስህብነቱን ለማሳደግ እየተሠራ ነው ብለዋል።   ከምስራቅ ሐረርጌ ዞን በተጨማሪም ከድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር እና ሐረሪ ክልል ጋር በመሆን በተለያዩ ዘዴዎች የማስተዋወቅ ሥራ እየተሠራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከባሕር ጠለል በላይ 3 ሺህ 440 ሜትር ከፍታ ያለው ደባል ሞቲ ጋራ በተፈጥሯዊ አቀማመጡ የጎብኚዎችን ዓይን የሚስብ መሆኑን ገልጸው፤ በዚህም ፓርኩን ለሀገር ውስጥና ውጭ ጎብኚዎች ምቹ ለማድረግና የአገልግሎት መስጫ ሎጆችን ለመገንባት ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። የኦሮሚያ ደንና ዱር እንስሳት ድርጅት የሐረርጌ ቅርንጫፍ በምዕራብና ምስራቅ ሐረርጌ ዞኖች ፓርኮች፣ የኢኮ ቱሪዝምና የተለያዩ መስህቦችን ያካተተ ከ77 ሺህ ሄክታር በላይ የደን ክልል ያስተዳድራል።
መንግስት ያመቻቸልንን የስራ ዕድል በመጠቀም ባስፋፋነው ስራ ሌሎችን ተጠቃሚ ማድረግ ችለናል
Jul 11, 2026 142
ሀዋሳ ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦መንግስት ያመቻቸላቸውን የስራ ዕድል በመጠቀም ባስፋፉት ስራ ሌሎችን ተጠቃሚ እያደረጉ መሆናቸውን በሲዳማ ክልል ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ገለጹ፡፡ የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ በተፈጠረው ምቹ የሥራ ዕድል ተጠቅመው በርካቶችን ወደ መቅጠር የደረሱ ስራ ፈጣሪዎች መኖራቸውን ጠቅሶ፣ በቀጣይም ይህ ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጿል። ወጣቶቹ እንደገለፁት፤ መንግስት ባመቻቸላቸው የብድርና የመስሪያ ቦታ በመጠቀም ስራቸውን በማስፋፋት ለሌሎች የስራ ዕድል ፈጥረዋል። በክልሉ በአለታ ወንዶ ከተማ የ”ጊዮን ሻማ አምራቾች ማህበር” አባል ወጣት ኤደን ማቲዎስ እንደገለጸችው፤ በተሰጣቸው አጭር የሥራ ፈጠራ ስልጠና፣ መነሻ ብድር፣ የባንክ ብድር አቅርቦት እንዲሁም የመስሪያና መሸጫ ቦታ ታግዘው አምስት ሆነው ወደ ሻማ ማምረት ሥራ መግባታቸውን ገልጻለች። ወደ ሥራ ከገባ ሦስት ዓመት የሆነው ማህበሩ ስኬታማ በመሆን ከመንግሥት የወሰዱትን 150 ሺህ ብር ብድር መመለሱንና ለ10 ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር አሁን ላይ አጠቃላይ ሀብታቸው ወደ አንድ ሚሊዮን ብር መድረሱን ተናግራለች። ከተስፋ መቁረጥ ሕይወት ወጥተው ዛሬ ላይ ከራሳቸው አልፈው ቤተሰብንና ሌሎችን ወደ መቅጠር መድረሳቸውን ገልጻ፤ ወጣቶች የመንግሥትን ድጋፍ እንደ መነሻ በመጠቀም በትጋት በመስራት መለወጥ እንደሚችሉ አመልክታለች።   ሌላው በጩኮ ከተማ በአገልግሎት ዘርፍ በመሰማራት ውጤታማ መሆናቸውን የተናገረው የ”እያየን ካፌና ጌም ዞን ማህበር” ሰብሳቢ ወጣት ሳሙኤል ተስፋ፤ መንግሥት ባመቻቸላቸው የ200 ሺህ ብር ብድርና የመስሪያ ቦታ ታግዘው ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግሯል። ሥራቸው በአጭር ጊዜ ውጤታማ በመሆኑ በሕይወታቸው ለውጥ ማየታቸውንና ለ32 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ጠቅሶ፣ አሁን ላይ አጠቃላይ ሀብታቸው ከ8 ሚሊዮን ብር በላይ መድረሱን ነው የገለጸው። በሐዋሳ ከተማ አስተዳደር እየተካሄደ ባለው የ4ኛው ዙር የኮሪደር ልማት ስራ በአረንጓዴ ልማት ተደራጅተው እንዲሰማሩ አስተዳደሩ ባመቻቸላቸው ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገረው ደግሞ ወጣት ግዛው ግርማ ነው። በሚያገኙት ገቢ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን እየደገፉ ሲሆን፤ አሁን ላይ ወጣቱን በልማት በማሳተፍ በፍትሐዊነት ተጠቃሚ ለማድረግ መንግሥት እያደረገ ባለው ጥረት መደሰቱንም ተናግሯል። የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ከፍያለው ከበደ፤ በክልሉ በከተማና በገጠር ያሉትን አማራጮችና ጸጋዎችን በተቀናጀ መንገድ በመጠቀም፣ የወጣቱን የሥራ ዕድል ፈጠራ ለማጠናከር የተደረጉ ጥረቶች ውጤታማ ናቸው ብለዋል።   በተለይ የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ዕድሎችን በማስፋት ረገድ መንግሥት የሰጠው ትኩረት ውጤት እያስገኘ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
የአርባ ምንጭን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት አቅሞች በመለየት በአጭር ጊዜ ውስጥ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የሚያስደንቁ ናቸው
Jul 11, 2026 123
አርባ ምንጭ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ የአርባ ምንጭን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት አቅሞች በመለየት በአጭር ጊዜ ውስጥ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የሚያስደንቁ መሆናቸውን የከተማዋ ነዋሪዎች ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሰሞኑን በአርባ ምንጭ ከተማና አካባቢው በመገኘት የገጠር ኮሪደርን ጨምሮ በከተማዋ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን መርቀው ስራ አስጀምረዋል። በቆይታቸው የተለያዩ የልማት ስራዎችን ተዘዋውረው የጎበኙ ሲሆን በአርባ ምንጭ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ከሀገርም ባለፈ ለጎረቤት ሀገራት ጭምር የሚጠቅሙ መሆናቸውን ተናግረዋል።   በከተሞችም ይሁን በገጠር ዜጎችን የሚጠቅሙና ሀገርን የሚለውጡ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን አንስተው ለኢትዮጵያ እድገትና ብልጽግና ስኬት የመንግስት ጥረት ይቀጥላል ብለዋል። በአርባ ምንጭ የተከናወኑ የልማት ፕሮጀከቶችን በተመለከተ ኢዜአ ያነጋገራቸው የከተማዋ ነዋሪዎች የአርባ ምንጭን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት አቅሞች በመለየት በአጭር ጊዜ ውስጥ የተከናወኑ የልማት ስራዎች የሚያስደንቁ መሆናቸውን አንስተዋል። ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል አቶ ተዘራ ቀፃዮ፤ በአርባ ምንጭ ከተማና አካባቢዋ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተገንብተውና ተጠናቀው ለአገለግሎት የበቁ ፕሮጀክቶች የመንግስትን የልማት ትጋት በተግባር የሚያሳዩ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሌላኛዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ ድንበሯ ቱሉ፤ አርባ ምንጭ ከተማ ከተቆረቆረች ረጂም ዓመታት ቢሆናትም ልማት እና እድገቷ እምብዛም እንደነበር አንስተዋል። በቅርቡ የተከናወኑ የልማት ስራዎች ግን እስካሁን ለምን መስራት አልተቻለም የሚል ቁጭት የሚፈጥሩ ስለመሆናቸው ተናግረው በዚህ ረገድ መንግስት እያደረገ ላለው ጥረት አመስግነዋል። በከተማዋ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ እየተገነቡ ያሉ የልማት ስራዎች የከተማዋን ዕድገት ከማፋጠን ባለፈ ለጉብኝትም ይሁን ኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት ነው ብለዋል። የከተማዋ ዕድገትና የሚታየው ለውጥ ለእንግዶች ብቻ ሳይሆን ለነዋሪዎችም አስደናቂ መሆኑን ተናግረው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ለማስቀጠል ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል። አቶ ግርማ ጉንሤ የተባሉ አስተያየት ሰጪ በበኩላቸው የአርባ ምንጭ ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ለኑሮ ምቹ እና ጽዱ ከማድረግ ባለፈ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴን እያሳለጠ መሆኑን ገልጸዋል።   በከተማዋ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ከተማዋ ባላት ፀጋ ልክ እንድታድግ እያስቻላት ነው ያሉት ደግሞ የአርባ ምንጭ ከተማ ከንቲባ መስፍን መንዛ (ዶ/ር) ናቸው። ሰው ተኮር እሳቤ ያለው የለውጡ መንግስት ከተሞችን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የሰነቀው ራዕይ የአርባ ምንጭ ከተማ ፀጋዎች ተገልጠው ወደ ሀብትነት እንዲቀየሩ ማስቻሉን ጠቅሰዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ እየተገነባ ያለው ከ20 ኪሎ ሜትር በላይ የተቀናጀ የኮሪደር ልማት አብዛኛው እየተጠናቀቀ እንደሚገኝም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የፋይናንስ ተደራሽነትን በማስፋትና በዘርፉ የሴቶችን አመራርነት ለማሳደግ እየሰራ ነው
Jul 11, 2026 576
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የፋይናንስ ተደራሽነትን በማስፋትና የሴቶች አመራር ውክልናን በማሳደግ የፋይናንስ አካታችነትን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ መሆኑን የባንኩ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በሁሉም ባንኮች ያለውን የሴቶች የፋይናንስ አካታችነት በየጊዜው መሻሻሉን መከታተል የሚያስችለውን ሁለተኛውን የሴቶች የፋይናንስ አካታችነት ስኮርካርድ ይፋ አድርጓል።   እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ኢኒሼቲቭ የሆነው የኢትዮጵያ ሴት የፋይናንስ ባለሙያዎች ኔትወርክ- (NEWFin) በአመራርና በመሠረታዊ የፋይናንስ ትምህርት የሰለጠኑ አንድ ሺህ ወጣት ሴት የፋይናንስ ባለሙያዎችን አስመርቋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ በሁለተኛው የሴቶች የፋይናንስ አካታችነት ስኮርካርድ ግምገማ 32 የሚሆኑ ባንኮች ማለፋቸውን ገልጸዋል። በዚህም የሴቶች የፋይናንስ ተጠቃሚነት ከባለፈው ዓመት መሻሻል ማሳየቱን አንስተው፣ አሁንም ይበልጥ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በትኩረት መስራት እንደሚገባ አመልክተዋል።   በቀጣይም የብድር መጠን ክፍፍልን ማሳደግና የስራ ፈጠራን ማቀላጠፍ ላይ ማተኮር እንደሚገባ አስታውቀዋል። የዘምዘም ባንክ ዋና ስራ አስኪያጅ እና የኒውፊን (NEWFin) ሊቀ-መንበር መሊካ በድሪ በበኩላቸው፤ ዛሬ የተመረቁት አንድ ሺህ ወጣት ሴት የፋይናንስ ባለሙያዎች የነገ የፋይናንስ ዘዋሪዎችና አመራሮች መሆናቸውን ገልጸዋል። አካታች የሆነ የፋይናንስ ስርዓት ለመፍጠር ያለንን ቁርጠኝነት በማጠናከር የበለጸገች ሀገር ለመገንባት በጋራ እንሰራለን ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ግብርን በወቅቱ በመክፈል የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ የበኩላችንን እየተወጣን ነው
Jul 11, 2026 221
ሆሳዕና፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱ በመክፈል በአካባቢው የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን የሆሳዕና ከተማ ግብር ከፋዮች ገለፁ። የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ጽሕፈት ቤት በ2019 በጀት ዓመት ከ3 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ከመደበኛና ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ለመሰብሰብ አቅዶ ወደ ተግባር መግባቱንም አስታውቋል። የከተማዋ ግብር ከፋዮች እንደገለፁት፤ ግብርን በወቅቱ መክፈል ለልማት ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ በማግኘት ተጠቃሚ ለመሆን ያስችላል። በከተማው የአራዳ ቀበሌ ነዋሪና የደረጃ "ሀ" ግብር ከፋይ አቶ ፀጋዬ በላቸው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱ በመክፈል በአካባቢው የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ አድርገዋል። በከተማው የሴች ዱና ቀበሌ ነዋሪዋና የደረጃ "ለ" ግብር ከፋይ ሐኒያ ኤልያስ በበኩሏ፤ የከተማውን ነዋሪዎች ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግራለች። የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ግብርን በወቅቱ መክፈል የልማት ጥያቄን ለመመለስና ከራስ ለራስ ልማት የሚውል በመሆኑ፣ የዜግነት ግዴታዋን መወጣት ስለመቻሏም ገልጻለች። በከተማው የሕዝብን ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች እንዲጠናከሩ ግብር ከፋዩ ማኅበረሰብ የሚጠበቅበትን ግብር በወቅቱ መክፈል አለበት ያሉት ደግሞ የደረጃ "ለ" ግብር ከፋይ የሆኑት አቶ ኤፍሬም አበራ ናቸው። ግብርን በወቅቱ መክፈል በሥነ ምግባር የታነጹ ዜጎችን ለማፍራት የሚረዱ የትምህርት ተቋማትን ለማስፋፋት፣ ጽዱ፣ ውብና ማራኪ አካባቢን ለተተኪው ትውልድ ለማስተላለፍ ያለው ሚና ከፍተኛ ስለመሆኑም አስረድተዋል። የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አውላቸው ዮሐንስ እንደገለፁት፤ በከተማው የገቢ አማራጭን በማስፋት የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰሩ ባሉ ሥራዎች ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል። ጽሕፈት ቤቱ በ2018 በጀት ዓመት ከመደበኛና ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች ከ2 ነጥብ 36 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። በ2019 በጀት ዓመት ከመደበኛና ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ከ3 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ትግበራ መገባቱንም ገልጸዋል።
የኑሮ ውድነትን ማረጋጋት የሚያስችሉና የገበያ ተደራሽነትን የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jul 11, 2026 334
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 4/2018(ኢዜአ)፦ የኑሮ ውድነትን ማረጋጋት የሚያስችሉና የገበያ ተደራሽነትን የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸሙን የሚገመግም የሴክተር ጉባኤ በሀዋሳ ያካሄደ ሲሆን፣ በቀጣይ በጀት ዓመት የትኩረት ነጥቦች ላይም ውይይት ተደርጓል።   ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደተናገሩት የንግድ ዘርፉን በማዘመን በኩል የተከናወኑ ውጤታማ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ጊዜንና ጉልበትን የሚቆጥቡ የዲጂታል አማራጮችን የማስፋት ሥራ በትኩረት መሰራቱንና አበረታች ውጤት መመዝገቡን ጠቅሰው የተገኙ መልካም ውጤቶች እንዲሰፉ ይደረጋል ብለዋል። የሸማቹንና ሻጩን በቀጥታ በማገናኘት ገበያን በማረጋጋት በኩል ቁልፍ ሚና እየተጫወቱ የሚገኙ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን የማጠናከርና ደረጃቸውን የማሻሻል ሥራም በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። የግብይት ማዕከላትን የማስፋት፣ የምርት ጥራትና ዋጋን ማዕከል ያደረገ የገበያ ቁጥጥር በአዲሱ በጀት ዓመት በልዩ ትኩረት ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል መሆኑንም አንስተዋል። በተጨማሪም የኑሮ ውድነትንና ገበያን ማረጋጋት የሚያስችሉ፣ የገበያ ተደራሽነትን የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ ነው ያሉት። ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል የአፋር ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ አህመድ አብዱልቃድር በክልሉ የገበያ ተደራሽነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት አበረታች መሆናቸውን ገልጸዋል።   በቀጣይም የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ደረጃቸውን ለማሻሻል በትኩረት ይሰራል ብለዋል። በክልሉ በበጀት ዓመቱ በንግድ ዘርፉ በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት ለመስጠት የተደረጉ ጥረቶች ስኬታማ መሆናቸውን ያነሱት ደግሞ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ባዩሽ ተስፋዬ (ዶ/ር) ናቸው።   በክልሉ ከ190 በላይ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች መገንባታቸውን አንስተው በተያዘው በጀት ዓመት ይህንን የማስፋት ሥራ ይሰራል ሲሉ ገልጸዋል።
በቡና ልማት ላይ የተደረገልን ሙያዊ ድጋፍ ተጠቃሚ አድርጎናል -አርሶ አደሮች
Jul 11, 2026 336
ነቀምቴ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን ባለፉት ዓመታት የቡና ልማትን ለማሳደግ የሚደረገው ድጋፍና ሙያዊ እገዛ ተጠቃሚ አድርጎናል ሲሉ ቡና አምራች አርሶ አደሮች ተናገሩ። በዞኑ የጉቶ ጊዳ ወረዳ አርሶ አደር ሀብታሙ ፍቃዱ፤ "ከጥቂት ዓመታት ወዲህ ለቡና ምርት በተሰጠው ትኩረትና የሚደረገውን ሙያዊ ድጋፍን በመጠቀም ጥራቱን የጠበቀ ምርት ማምረት ጀምረናል፤ በዚህም ይበልጥ ተጠቃሚ እየሆንን ነው" ብለዋል። በአሁኑ ወቅት የቡና ምርት ልማትና ጥራት በየጊዜው እያደገ በመምጣቱ፣ ጥራቱን የጠበቀ ምርት በማቅረብ በገበያው ተወዳዳሪ ለመሆን እየሰሩ መሆኑንም ተናግረዋል። በቀጣይም በዓለም ገበያ ተፈላጊ የሆኑ የቡና ዝርያዎችን በማልማት ስራቸውን ይበልጥ ለማሻሻል ማቀዳቸውን ገልጸዋል።   ሌላኛው የቢሎ ቦሼ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ደረጄ አርፍሳ በበኩላቸው፤ ዘንድሮ ያረጁ የቡና ተክሎችን በመንቀል እና በመጎምደል እንዲሁም አዳዲስ ምርጥ ዝርያ ያላቸው ችግኞችን እየተከሉ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በጥራት መጓደል ምክንያት በሚያመርቱት ልክ ለገበያ ማቅረብ እንዳልቻሉ ያስታወሱት አቶ ደረጄ፣ አሁን ላይ ግን ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን ማቀዳቸውን ጠቁመዋል። የምስራቅ ወለጋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት የቡናና አትክልት ልማት ቡድን መሪ አቶ አስፋው መኮንን በበኩላቸው፤ በዞኑ በየደረጃው በተሰጠ ስልጠና እና በተደረገ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ፣ ጥራቱን የጠበቀ ቡና እየተመረተ መሆኑን ተናግረዋል።   አርሶ አደሮች ከተከላ እስከ ምርት አሰባሰብ ያለውን የጥራት አጠባበቅ ሂደት እንዲረዱ እና በቴክኖሎጂ የተደገፈ የአመራረት ስልትን በመጠቀም ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ ትኩረት መደረጉንም ገልጸዋል። ከ96 ሄክታር በላይ መሬት ላይ የሚገኝ ያረጀ ቡና ተነቅሎ በአዲስ ችግኝ የተተካ ሲሆን፣ 320 ሄክታር መሬት ላይ የሚገኝ ያረጀ ቡና ደግሞ መጎንደሉን ተናግረዋል። ዘንድሮም በመንግስትና በግል የቡና ችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች ከ300 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኝ የተዘጋጀ ሲሆን፣ የተከላ ስራውም እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።
በባሌ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራ አማራጮችን በማስፋት የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል
Jul 11, 2026 394
ሮቤ፤ ሐምሌ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራ አማራጮችን በማስፋት የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተሰሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት መታየቱን የዞኑ የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከ89 ሺህ 500 ለሚበልጡ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩ ተመላክቷል። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ተሾመ ለሚ በተለይ ለኢዜአ እንዳሉት፣ በዞኑ የሥራ ዕድል ፈጠራ አማራጮችን በማስፋት የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተሰሩ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት ተገኝተዋል።   በዞኑ በተያዘው የበጀት ዓመት ከ89 ሺህ 500 ለሚበልጡ ወጣቶች በተለያዩ መስኮች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል። ወጣቶቹ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው በከተማ ግብርና ልማት፣ በእንጨትና ብረታ ብረት፣ በዶሮና እንስሳት እርባታ ዘርፎች መሆኑን ገልጸዋል። ወጣቶቹ በተሰማሩባቸው የሥራ መስኮች ውጤታማ እንዲሆኑ ከ964 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር የተመቻቸላቸው ሲሆን፣ 4 ሺህ 540 ሄክታር የእርሻ መሬት እንዲያኙ መደረጉን አክለዋል። ለእነዚሁ በእርሻ ሥራ የተሰማሩ ወጣቶች በተመቻቸው ብድር በመጠቀም 50 የእርሻ ትራክተሮች የተገዙላቸው መሆኑን አመልክተዋል። የአጋርፋ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አብዱልቃድር ኡስማን በበኩላቸው፣ በወረዳው የከተማ ግብርናና የጎጆ ኢንዱስትሪ ኢኒሼቲቭ የበርካታ ወጣቶች የገቢ ምንጭ እየሆነ መጥቷል ብለዋል።   በወረዳው በበጀት ዓመቱ በዘርፉ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለሆኑ 10 ሺህ ለሚበልጡ ወጣቶች ከ185 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር እንዲያገኙ መደረጉን ተናግረዋል። በአጋርፋ ወረዳ የሥራ ዕድል ተጠቃሚዎች መካከል አደም አብደላ በሰጠው አስተያየት፣ በእንጨትና ብረታ ብረት ሥራ በመሰማራት ውጤታማ በመሆን ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ተናግሯል። በቀጣይም ወደ ተሻለ የኢንቨስትመንት ዘርፍ ለመሸጋገር ጠንክሮ እንደሚሠራ ገልጿል።   በከተማው በወተት ላሞች እርባታ በመሰማራት ውጤታማ እየሆነ መምጣቱን የተናገረው ደግሞ ወጣት አብዱለጢፍ አብዱልመናን ነው። በሥራው ውጤታማ በመሆን ቤተሰቡን ከማስተዳደር ባለፈ ጥሪት ማፍራት መጀመሩን ተናግሯል። በባሌ ዞን ባለፈው የበጀት ዓመት 75 ሺህ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሮ እንደነበር ተጠቅሷል።
በከተማው በአዲሱ በጀት ዓመት 12 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደተግባር ተገብቷል
Jul 10, 2026 785
‎‎ሀዋሳ፤ ሐምሌ3/2018(ኢዜአ)፡-በሀዋሳ ከተማ አስተዳደር በአዲሱ በጀት ዓመት 12 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደተግባር መገባቱን የከተማ አስተዳደሩ ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በከተማው ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የነዋሪዎችን የመሠረተ ልማት እና የአገልግሎት አቅርቦት ጥያቄዎች ለመመለስ ትኩረት መሰጠቱም ተመላክቷል። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ መልኩ ማርቆስ ለኢዜአ እንደገለጹት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በከተማው ከ7 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ የዕቅዱን 102 ፐርሰንት ማሳካት ተችሏል፡፡ በ2019 ግብር ዘመን12 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደተግባር መገባቱን ገልፀው ከሐምሌ 1 ጀምሮ ገቢ የመሰብሰብ ሥራው መጀመሩን ጠቅሰዋል፡፡   ባለፉት ሁለት ዓመታት የገቢ አሰባሰብ ሥራው በቴክኖሎጂ መታገዙ፣ የባለሙያዎች አቅም መገንባቱና የገቢ ምንጮችን ማስፋት በመቻሉ ገቢን ማሳደግ ተችሏል ብለዋል፡፡ በተያዘው የግብር ዘመንም የተጨማሪ እሴት ታክስ ገቢን የማሳደግ፣ ከቅጥር የሚገኝ ገቢን እና የአከራይ ተከራይ ገቢን አሟጦ የመሰብሰብ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አቶ መልኩ አስረድተዋል፡፡ በከተማ አስተዳደሩ ካለፉት ሁለት ዓመታት ጀምሮ ከጥሬ ገንዘብ ንክኪ ነፃ የሆነ የገቢ አሰባሰብ ሥርዐት በመዘርጋት በባንክ የክፍያ ማረጋገጫ ብቻ ገቢ እየተሰበሰበ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ ከዚህ ዓመት ጀምሮም የባንክ ክፍያን በማስቀረት በቴሌ ብር፣ በሞባይል ባንኪንግ እና ሌሎች ዘመናዊ የክፍያ አማራጮች ብቻ ገቢን ለመሰብሰብ የሚያስችሉ ቅድመ ዝግጅቶች ተደርገው ወደ ሥራ መገባቱን አስረድተዋል፡፡ በከተማው ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የነዋሪዎችን የመሠረተ ልማት እና የአገልግሎት አቅርቦት ጥያቄዎች ለመመለስ ትኩረት መሰጠቱንም አመልክተዋል። ከሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ እየተካሄደ ባለው የገቢ አሰባሰብ ሂደት ግብር ከፋዮች ግብራቸውን እየከፈሉ እንደሚገኙም አቶ መላኩ ጠቁመዋል፡፡   ከእነዚህ መካከል በታቦር ክፍለ ከተማ በሸቀጣሸቀጥ ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩት ወይዘሮ መስከረም አስፋው በየዓመቱ ግብራቸውን በወቅቱና በታማኝነት የመክፈል ልምድ እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡ ከዜጎች የሚሰበሰበው ገቢ በከተማዋ ለሚከናወኑ የልማት ሥራዎች እንደሚውል በመረዳታቸው በራሳቸው ተነሳሽነት ግብራቸውን በወቅቱ እንደሚከፍሉ ተናግረዋል፡፡ በግብር ሰብሳቢው አካል የሚሰጠው አገልግሎት በቴክኖሎጂ የታገዘና ከጊዜ ወደ ጊዜ ቅልጥፍናው እየጨመረ የመጣ በመሆኑ ያለ እንግልት ግብራቸውን በቀላሉ መክፈል እንደቻሉም ጠቁመዋል፡፡   በሀዋሳ መናኸሪያ ክፍለ ከተማ በእንግዳ ማረፊያ የአገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ኢያሱ በገጄ ግብር ለሀገራችን የምንከፍለው የዜግነት ግዴታችን ነው ብለዋል፡፡ የከተማዋ የልማት ሥራ ጥቅሙ ለነዋሪው እንደሆነ ጠቅሰው ልማቱ እንዲፋጠን ግብራቸውን በአግባቡና በወቅቱ በመክፈል ሀላፊነታቸውን እየተወጡ መሆኑን ገልፀዋል፡፡  
ቢሮው የአገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የተገልጋዩን እርካታ ማሳደግ ችሏል
Jul 10, 2026 661
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 3/ 2018 (ኢዜአ):-የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ የአገልግሎት አሰጣጡን በቴክኖሎጂ በመደገፍና አዳዲስ አሰራሮችን በመዘርጋት የተገልጋዩን እርካታ ማሳደግ መቻሉን አስታወቀ። ቢሮው በ2018 በጀት ዓመት የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት ያከናወናቸውን ተግባራት፣ የቢሮውን የለውጥ ጉዞና የተገኙ ስኬቶችን የሚያሳይ ኤግዚቢሽንም በዛሬው ዕለት በይፋ ከፍቷል።   የቢሮው የጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳነ ሱሌ በኤግዚቢሽኑ መክፈቻ ላይ እንደገለጹት፤ ቢሮው የግብር ከፋዩን እንግልት ለመቀነስና ግልጽነትን ለመፍጠር በርካታ የሪፎርም ስራዎችን አከናውኗል። ወደ 24 የሚጠጉ አሰራሮች መዘርጋታቸውን ይህንንም በማሳተም ለተገልጋዩ ማህበረሰብ ተደራሽ መደረጉንና ከግብር ከፋዩ ሕብረተሰብ ጋር ተደጋጋሚ ውይይቶች መደረጋቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት መሰራቱን ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት በቢሮው ስር ባሉ 17ቱም ቅርንጫፎች የሚገኙ ከሰባት ሺህ በላይ ሰራተኞችን መቆጣጠር የሚያስችል የቴክኖሎጂ አሰራር መዘርጋቱን ጠቁመዋል፡፡ በዚህም የአገልግሎት አሰጣጡ እንዴት እየተከናወነ እንደሚገኝ ዋና ቢሮ ሆኖ በቀጥታ መከታተል የሚያስችል የቁጥጥር ስርዓት መዘርጋቱንም ጠቁመዋል፡፡ በኤግዚቢሽኑ መክፈቻ ስነ-ስርዓት ላይ የተገኙት የአዲስ አበባ የንግድ እና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ዘሃራ መሐመድ በበኩላቸው፤ ከቢሮው ጋር እየተደረገ ያለው የተቀናጀ አሰራር አዎንታዊ ውጤት እያመጣ መሆኑን ገልጸዋል።   በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ በተደረገው የጋራ ጥረትና ቅንጅታዊ አሰራር፣ ከነጋዴው ማህበረሰብ የተነሱ የተለያዩ ቅሬታዎችን በጋራ በመገምገም 620 ለሚሆኑ ነጋዴዎች ለገጠሟቸው ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ እንዲያገኙ ማድረግ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡      
ተምሳሌቶቹ የቢሾፍቱ ከተማ የሌማት ትሩፋት ተጠቃሚዎች
Jul 10, 2026 568
የሌማት ትሩፋት ሀገራዊ ውጤት እና በመርሃ ግብሩ ህይወታቸውን ያሻሻሉ የቢሾፍቱ ነዋሪዎች ለብዙ ኢትዮጵያውያን ወተት፣ እንቁላል፣ ማርና ሥጋ በምግብ ገበታ የማይገኙ፣ ለረጅም ዓመታት የቅንጦት ያህል የሚታዩና በቂ ምርት ባለመኖሩም በገበያ ላይ በስፋት የማይገኙ ነበሩ። ይህንን እውነታ ለመቀየርና የዜጎችን የሥርዓተ ምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ጥቅምት 24 ቀን 2015 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተጀመረው የሌማት ትሩፋት ሀገራዊ መርሃ ግብር ዛሬ ላይ ትልቅ ተስፋና ተጨባጭ ውጤት እያሳየ ይገኛል። ቀደም ሲል ትኩረት አጥቶ የነበረውን የእንስሳት ተዋጽኦ ልማት በቅንጅትና በቴክኖሎጂ በመደገፍ ረገድ በአካባቢው ተጨባጭ ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል። በግብርና ሚኒስቴር መረጃ መሠረት መርሃ ግብሩ ከመጀመሩ በፊት የነበረው 7 ነጥብ 1 ቢሊዮን ሊትር የወተት ምርት ዘንድሮ 15 ነጥብ 7 ቢሊዮን ሊትር መድረሱ፣ ቀደም ሲል በዓመት ይሰራጭ የነበረው የዶሮ ጫጩት ከ26 ሚሊዮን ወደ 184 ሚሊዮን ማደጉ እንዲሁም የእንቁላል ምርት ከ3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ወደ 11 ነጥብ 7 ቢሊዮን ከፍ ማለቱ የዚሁ አገራዊ ስኬት ማሳያዎች ናቸው።   ይህ የተጀመረው አበረታች ሂደት እንደ ወተት፣ ማር፣ ሥጋ፣ አሳ እና እንቁላል ያሉ ምርቶች የቅንጦት ሳይሆኑ የዜጎች የዕለት ተዕለት የሥርዓተ ምግብ አካል እንዲሆኑ በማስቻል ረገድም ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። በቢሾፍቱ ከተማና አካባቢዋ ለሚኖሩ በርካታ ዜጎች የአመጋገብ ሥርዓትን ከመቀየር ባለፈ፣ የኢኮኖሚ አቅማቸውን የለወጠ የሕይወት ጉዞን ፈጥሮላቸዋል። አቶ ከፈለኝ ጫላ ቀደም ሲል በመንግሥት ተቋም ተቀጥረው የሚሠሩ መደበኛ ሠራተኛ ነበሩ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ላይ ዜጎች እንዲሳተፉ ጥሪ ሲቀርብ ግን የቀደማቸው አልነበረም።   በተመቻቸላቸው የብድር አገልግሎት በመታገዝ በአንድ የወተት ላም ሥራቸውን ጀመሩ። ዛሬ ላይ ግን ታሪካቸው ሙሉ በሙሉ ተቀይሯል። የነበራቸውን ብቸኛ ላም ተንክባክበውና አርብተው በአሁኑ ወቅት የወተት ላሞቻቸውን ቁጥር 15 ማድረስ ችለዋል። "መንግሥት ያደረገልኝ ተከታታይ ድጋፍና ክትትል ለዚህ ውጤት እንድበቃ ትልቅ አስተዋጽኦ አበርክቶልኛል" ይላሉ አቶ ከፈለኝ። የራሳቸውን ኑሮ ከመቀየር ባለፈ፣ የሚያመርቱትን ወተት ለአካባቢው ማኅበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ገበያውን በማረጋጋት ረገድ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛሉ። በተጨማሪም በመስኩ ለሌሎች ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ችለዋል።   ሌላኛው በዚሁ መርሃ ግብር ሕይወታቸው የተቀየረው ሥራ ፈጣሪ አቶ ጌቱ ብሩ ናቸው። እሳቸው ደግሞ በተቀናጀ የዶሮና የዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ ላይ ነው የተሰማሩት። የሌማት ትሩፋት ያመጣላቸው በረከት ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ከመጥቀም አልፎ የንግድ አድማሳቸውን አስፍቶላቸዋል። ከልማቱ በሚያገኙት የምርት ውጤት የራሳቸውን ሆቴል መክፈት የቻሉ ሲሆን፣ ለበርካታ ዜጎችም አዲስ የሥራ ዕድል ፈጥረዋል።   "ለሆቴላችን የምግብ ግብዓት የሚሆነውን ምርት የምናቀርበው ከራሳችን የዶሮና የዓሣ እርባታ ማዕከል ነው" የሚሉት አቶ ጌቱ፣ ዘርፉ ሰፊና ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት የሚቻልበት መሆኑን ይመሰክራሉ። አቶ ጌቱ እቅዳቸው እዚህ ላይ ብቻ አያበቃም፤ በቀጣይ የሌማት ትሩፋት ምርቶችን እሴት ጨምረው ለከተሞች ከማቅረብ ባለፈ ወደ ውጭ ሀገር ለመላክና ለሀገር የውጭ ምንዛሬ የማስገኘት ውጥን አላቸው። ሌሎችም በዚህ ሥራ ላይ ቢሰማሩ ከራሳቸው አልፈው ሀገርንና ወገንን መለወጥ እንደሚችሉም ነው የጠቆሙት።   በተመሳሳይ በዶሮ እርባታ ሥራ ላይ የተሰማሩት አቶ ደረጄ አበበ መርሃ ግብሩ ከፍተኛ ገቢ እንዲያገኙ እንዳስቻላቸው ይናገራሉ። የዶሮ እንቁላል ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለአካባቢው ማኅበረሰብ በስፋት በማቅረብ የኑሮ ውድነቱን ለመቋቋም የበኩላቸውን እየተወጡ ይገኛሉ። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር)፥ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በርካታ ስኬቶች የተመዘገቡበትና የዜጎችን የምግብና ሥርዓተ ምግብ አቅም እያሳደገ የሚገኝ ኢኒሼቲቭ ነው ብለዋል።   ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የምታደርገውን ሀገራዊ ጥረት ለማሳካት የእንስሳት ሀብት ልማት ዘርፍ ያለው ሚና ከፍተኛ መሆኑንም ጠቅሰዋል። አክለውም፤ ኢኒሼቲቩ በቤተሰብ ደረጃ የዶሮ እርባታን ባህል እንዲሆን በማድረግ፣ በተለይም ሕፃናትና እናቶች የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ በማስቻል ረገድ መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑንና ምርቶችን በስፋት ለገበያ እንዲቀርቡ በማስቻል ረገድ ትርጉም ያለው ውጤት ማምጣቱን ገልጸዋል።    
በጎንደር ከተማ ወደ 49 ሺህ ለሚጠጉ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል ተፈጥሯል
Jul 10, 2026 516
ጎንደር፤ ሃምሌ 3/2018 (ኢዜአ)፡- በጎንደር ከተማ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 49 ሺህ ለሚጠጉ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል መፍጠር መቻሉን የከተማ አስተዳደሩ የስራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የከተማ አስተዳደሩ ሥራና ክህሎት መምሪያ ያለፈውን በጀት ዓመት የሥራ አፈፃፀም ግምገማና የ2019 ዓ.ም ዕቅድ ትውውቅ መድረክ ዛሬ በጎንደር ከተማ አካሄዷል።   የመምሪያው ኃላፊ አቶ አበበ ላቀው በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በከተማዋ በተካሄዱ የኢንዱስትሪ፣ የከተማ ግብርና፣ የንግድና አገልግሎት ዘርፎች ለወጣቱ የሥራ ዕድል ለመፍጠር በትኩረት ተሰርቷል። በዚህም በበጀት ዓመቱ ለ44 ሺህ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ በተደረገ ጥረት፣ ከ48 ሺህ 900 በላይ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ከዕቅድ በላይ መፈጸም መቻሉን ገልፀዋል። ከዕቅድ በላይ ማስመዝገብ የተቻለውም በተገኘው ሰላም ባለሀብቱ ተረጋግቶ ወደ ልማት በመግባቱና አመራሩና ባለሙያው የተጠናከረ ድጋፍ በማድረጋቸው መሆኑንም አብራርተዋል። ከአበዳሪ ተቋማት ጋር በመተባበርም ለ2 ሺህ 689 ኢንተርፕራይዞች 665 ሚሊዮን ብር ብድር በማሰራጨት ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። የሥራ ዕድሉን መፍጠር የተቻለውም በኮንስትራክሽን፣ በከተማ ግብርና፣ በአነስተኛ ንግድና ሌሎች የሥራ ዘርፎች መሆኑን አስረድተዋል። በተጨማሪም መምሪያው ከሥራ ዕድል ፈጠራ ጎን ለጎንም ለ856 ኢንተርፕራይዞች የኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን ድጋፍ በማድረግ ያሉባቸውን ችግሮች ለመፍታት ጥረት ማደረጉን ገልጸዋል። ከጎንደር ከተማ አስተዳደር መሬት መምሪያ ጋር በመተባበር በኮሪደር ልማት ለተነሱ 334 ግለሰቦች የመስሪያና የመሸጫ አገልግሎት መስጫ ሼድ በማስገንባት ማስረከብ መቻሉንም አክለዋል።   በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የጎንደር ከተማ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኃላፊ አቶ ግርማይ ልጅዓለም በበኩላቸው፤ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በሥራ ዕድል ፈጠራ አበረታች ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። ይህም የከተማው አስተዳደር የወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራ ስራን በዋነኝነት ይዞ በየጊዜው እየገመገመና የቀጣይ አቅጣጫ በማስቀመጥ በመስራቱ የመጣ ውጤት መሆኑን አስረድተዋል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም