ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በአዲስ አበባ የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ያስቻሉ ስኬታማ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል
May 8, 2026 229
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ያስቻሉ ስኬታማ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ጉባኤዉን በዓድዋ ድል መታሰቢያ የምክር ቤቱ መሰብሰቢያ አዳራሽ አካሂዷል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና የከተማው ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማብራሪያቸው፤ በመዲናዋ ለህዝብ በተገባው ቃል መሠረት በሁሉም መስክ ዕድገትን የሚያፋጥን የልማት ስኬት መመዝገቡን አብራርተዋል። ለአብነትም የነዋሪዎች የመኖሪያ ቤት ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት በመንግስት፣ በመንግስትና በግል አጋርነት፣ በሪል እስቴት፣ በግለሰብና በግለሰብ-ግለሰብ አጋርነት በርካታ ቤቶች መገንባታቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም በፕሮጀክት ግንባታ የተፈጠረውን ውጤታማ ስትራቲጂያዊ አፈፃጸም በማጎልበት የነዋሪዎችን የመኖሪያ ቤት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በማህበራዊ ዘርፍም በጤና መከላከልና አክሞ ማዳን የአገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት የሚያፋጥን ውጤታማ የጤና ተቋማት ግንባታ ዕውን ማድረግ እንደተቻለ አስረድተዋል። በዚህም በነባር ሆስፒታሎች ማስፋፊያና አዳዲስ የጤና ተቋማት ግንባታ የእናቶችና ሕፃናትን ጨምሮ የዜጎች ጤና አገልግሎት ጥራትንና ተደራሽነትን የሚያስጠብቅ መሠረተ ልማት መገንባቱን አንስተዋል። የዋጋ ግሽበትን ለመከላከል በተወሰዱ እርምጃዎችም የዋጋ ግሽበትን ወደ ነጠላ አሃዝ ዝቅ ማድረግ ያስቻለ አበረታች ውጤት መመዝገቡን ጠቅሰዋል። በዚህም የነዋሪዎችን የኑሮ ጫና በቅዳሜና እሁድ ገበያና የገበያ ማዕከላት ሌሎች የምርት አቅርቦት ሥራዎች አቅርቦትና ፍላጎትን ማመጣጠን ያስቻለ ሥራ መሰራቱን አንስተዋል። የመዲናዋን የትራንስፖርት አገልግሎት ለማሳለጥ በተከናወኑ ተግባራትም በተሽከርካሪ አቅርቦት፣ በመኪና ማቆሚያና በብዙኅን ትራንስፖርት ዘርፍ ወሳኝ ስራ መሰራቱን አንስተዋል። በመጭው አዲስ ዓመትም 500 የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ወደ ሥራ ለማስገባት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት የ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ጉባኤ በከንቲባ አዳነች አቤቤ የቀረቡለትን ልዩ ልዩ ሹመቶችን ያጸደቀ ሲሆን የምክር ቤቱን የፍትሕና መልካም አስተዳደር ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢና የአዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት እጩዎች እንዲሁም የአዲስ ሚዲያ ኔትዎርክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሰለሞን ዲባባን ሹመት አጽድቋል፡፡ በተጨማሪም ምክር ቤቱ የ9 ነጥብ 94 ቢሊየን ብር ተጨማሪ በጀት አጽድቋል፡፡
ኢትዮጵያ ታመርታለች፤ የተሟላ ሉዓላዊነቷን የማረጋገጥ ጉዞዋን አጠናክራ ትቀጥላለች
May 8, 2026 180
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ታመርታለች፤ የተሟላ ሉዓላዊነቷን የማረጋገጥ ጉዞዋን አጠናክራ ትቀጥላለች ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሀሳብ ላለፉት ስድስት ቀናት ሲካሄድ የቆየው አራተኛው የኢትዮጵያ ታምርት ዓለም አቀፍ ኤክስፖ የመዝጊያ መርኃግብር ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት ተካሂዷል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በዚህ ወቅት ባደረጉት ንግግር፤ በአምራች ኢንዱስትሪው የተመዘገቡ ተጨባጭ ውጤቶች የኢትዮጵያን ብልፅግና ያሳዩ ናቸው ብለዋል። በተለዋዋጭ የዓለም ሁኔታ የሀገርን ሉዓላዊነት አስጠብቆ ለመቀጠል ውድድሩን መምራት ካልሆነም ከዓለም እኩል መራመድ ይገባል ብለዋል። በዚህ የዓለም ሁኔታ ራሱን የቻለ ያሸንፋል ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በዚህ ረገድ አምራች ኢንዱስትሪው ወሳኝ ዓምድ መሆኑን ጠቅሰዋል። መንግስት ይሄንኑ በሚገባ በመረዳቱ ከመደመር ፍልስፍና እሳቤ የሚመነጩ፣ የፖሊሲ ነጻነትን የሚያጎናጽፉ የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ በመተግበር ሀገር ከነበረባት ስብራት አገግማ በዓለም አደባባይ ስሟ በበጎ እንዲጠራ እያስቻለ ነው ብለዋል። የሀገር ሉዓላዊነትና ነጻነት በሙሉነት የሚረጋገጠው በጥራት፣ በዓይነት እና በብዛት የኢንዱስትሪ ምርቶችን በራስ ዕውቀት፣ በራስ ክህሎት እና በራስ ቴክኖሎጂ ማምረት ሲችሉ መሆኑን ጠቁመዋል። የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ፣ ምቱ እና ትርታው ጤናማ ካልሆነ፣ በኢኮኖሚ ዘርፉም ሆነ በአጠቃላይ በማኅበራዊ እና ፖለቲካዊ ዘርፎች ላይ መዳከምን እንደሚፈጥር ተናግረዋል። መንግሥት በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ የታለመውን ዘላቂ ዕድገት እና ተወዳዳሪነት በማረጋገጥ፣ ዘርፉ በኢኮኖሚው ውስጥ የሚያበረክተውን ድርሻ በፍጥነትና በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማሳደግ ፖሊሲዎችን ማሻሻሉን፣ አሠራሮችን መዘርጋቱን፣ የማበረታቻ ሥርዓት መፍጠሩን፣ አምራች ኢንዱስትሪውን የሚደግፍ ብሔራዊ ካውንስልም ማቋቋሙን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የዚህ ሪፎርም አካል መሆኑን በማንሳት በአራት ዓመታት ውስጥ ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ደርሷል ነው ያሉት። ከግብዓት አቅርቦት፣ ከመሠረተ ልማት ዝርጋታ፣ ከሎጅስቲክስ አገልግሎት፣ ከሰው ኃይል ልማት እና ምቹ የቢዝነስ ከባቢን ከመፍጠር አንጻር በርካታ ቅንጅታዊ ሥራዎች ተሠርተዋል ብለዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄም ሆነ በካውንስሉ በተሠሩ ሥራዎች የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም ማሻሻል ተችሏል ብለዋል፡፡ ተኪ ምርቶችን በብዛትና በጥራት ማምረት መጀመሩ ከወጪ ንግድ እና ከሥራ ዕድል ፈጠራ አንጻርም ብዙ ለውጦች መምጣታቸውን ነው ያነሱት። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የሥራ ባህልንና ምርታማነትን ማሻሻሉን፣ የሀገር ውስጥ ምርትን የመሸመት እና የመጠቀም ባህልን ማሳደጉንም ተናግረዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ አምራች ኢንዱስትሪው ከራሱ ዘርፍ ዕድገት ባሻገር እንደ ግብርና፣ ኮንስትራክሽን፣ ቱሪዝም እና ጤና ላሉ ሌሎች ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም ማኅበራዊ ዘርፎች መነቃቃት እያደረገ ያለው አስተዋጽዖ ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡ አምራች ኢንዱስትሪውን ከዚህ በላይ ለማሳደግ ኢንዱስትሪያዊ አመለካከት፤ ኢንዱስትሪያዊ ባለ ሀብት እና ኢንዱስትሪያዊ አመራር መኖር እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል። ጎንበስ ብሎ አፈር ነክቶ ከብረትና ከማዕድናት ጋር ታግሎ፣ ታሪክን መቀየር ያልተቻለው በዚህ የአመለካከት መዛነፍ የተነሣ ነው በማለት አሁን እሱን እየቀየርን እንገኛለን ብለዋል፡፡ በቀጣይ ዓመት ኤክስፖ የላቁ አዳዲስ እና የተሻሻሉ ምርቶች እንደሚቀርቡም ተስፋቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያም የማምረትና የተሟላ ሉዓላዊነቷን የማረጋገጥ ጉዞዋን አጠናክራ እንደምትቀጥል በአፅንኦት ተናግረዋል።
በዘንድሮው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ከ57 ቢሊዮን ብር በላይ የገበያ ስምምነት ተፈጽሟል
May 8, 2026 158
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ)፦በዘንድሮው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ከ57 ቢሊዮን ብር በላይ የገበያ ስምምነት መፈጸሙን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ፡፡ "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሀሳብ ሲካሄድ የቆየው የ2018 የኢትዮጵያ ታምርት ዓለም አቀፍ ኤክስፖ የመዝጊያ መርኃ ግብር ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት ተካሂዷል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ ራሷን መቻሏ የህልውና እና የሉዓላዊነት ጉዳይ እንደሆነ ገልጸዋል። አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን ለምርታማነትና ለፈጠራ መጠቀም መጪውን ዘመን መዋጀት መሆኑን ጠቅሰዋል። ለአብነት ያህል በአምስቱም ዘርፎች ከ350 በላይ ኢንዱስትሪዎች መሳተፋቸውን ጠቅሰው፤ ጀማሪ ድርጅቶችን ለማበረታታት በተደረገው ድጋፍ ምርታቸውን እንዲያቀርቡ መደረጉንም ገልጸዋል። በዚህ መርሃ ግብር 20 ስታርት አፖች የፈጠራ ስራቸውን ለጎብኚዎች ማቅረባቸውንም አክለዋል፡፡ አዳዲስ ፈጠራ የተጨመረባቸው የምርት ልማት ውድድሮች በ22 ኢንዱስትሪዎች ለእይታ መቅረባቸውን ጠቅሰው፤ በምግብ ቅምሻ 10 ድርጅቶች ከተለያዩ ግብዓቶች ያመረቷቸውን ልዩ ልዩ ምርቶች በተሳታፊዎች ማስመረጣቸውንም ተናግረዋል፡፡ ከኤክስፖው ከ12 ሺህ በላይ የግብይት ትስስሮች በአምራቾች መካከል መከናወናቸውንም ጠቁመዋል፡፡ በ16 የመንግስት ተቋማትና አምራች ኢንዱስትሪዎች መካከል በተደረገ ትስስር ከ57 ቢሊዮን ብር በላይ የገበያ ስምምነት መፈጸሙን ጠቅሰዋል። መንግሥት ለአምራች ዘርፉ የሰጠውን ትኩረት በኤክስፖው ማሳየት መቻሉን ገልጸዋል። አምራቾች ወደ አፍሪካ ገበያዎች ጭምር መግባት እንዳለባቸው አቅጣጫ የተቀመጠበት፣ የፋይናንስ አቅርቦትን ለማሻሻል ውሳኔ ላይ የተደረሰበት እንዲሁም በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታገዘ የምርት ሂደትን ለመጀመር መነሳሳት የተፈጠረበት ኤክስፖ ነው ብለዋል። በርካታ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ምርቶቻቸውን እንዲያስተዋውቁና ከከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች ጋር ትስስር እንዲፈጥሩ መደረጉንም ገልጸዋል። የቀጣዩ ዓመት የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ከግንቦት 5 እስከ 10 ቀን 2019 ዓ.ም ይካሄዳል ብለዋል።
በኤክስፖው የቀረቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን ማየታችን በራሳችን የመተማመን መንፈስና መነሳሳትን ፈጥሮብናል
May 8, 2026 172
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ)፦በአራተኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ የቀረቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን ማየታችን በራሳችን የመተማመን መንፈስና ለቀጣይ ሥራ መነሳሳትን ፈጥሮብናል ሲሉ ኤክስፖውን የጎበኙ ተማሪዎች ገለጹ፡፡ "ኢትዮጵያ ታምርት፤ ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሐሳብ ላለፉት ቀናት ሲካሄድ የቆየው አራተኛው አገር አቀፍ የኢንዱስትሪ ኤክስፖም በዛሬው ዕለት ተጠናቋል፡፡ ከተለያዩ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ ከ1 ሺህ በላይ ተማሪዎች ኤክስፖውን የጎበኙ ሲሆን፤ ጉብኝቱ ለተማሪዎች ትልቅ የተስፋና የ"ይቻላል" መንፈስን ያሰረጸ ነው፡፡ በዚሁ ጊዜ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ተማሪዎች፤ በኤክስፖው የተመለከቷቸው የፈጠራ ስራዎችና ምርቶች ትልቅ መነሳሳትን እንደፈጠሩባቸው ገልጸዋል። ተማሪ ሮዛ ሃዱሽ እንዳለችውም ኢትዮጵያ ሌሎች አገራት የሚያመርቱትን ምርቶች ማምረት እንደምትችል በተግባር በማየቷ መደሰቷን ገልጻለች፡፡ ይህም " እኛ በቀጣይ በዘርፉ ተሰማርተን የአገራችንን ኢኮኖሚ ለማሳደግ እንድንሰራ የ'ይቻላል' መንፈስ ፈጥሮብናል" ብላለች። ተማሪ ራፍኤል በፍቃዱ እና ተማሪ ቡአዝ አዋድ በበኩላቸው፤ አገራቸው ምርቶችን ከውጭ ከማስገባት ይልቅ እዚሁ አምርታ ወደ ውጭ መላክ እንደጀመረች መገንዘባቸውን ገልጸዋል፡፡ይህም አገራዊ አቅም እያደገ መሆኑን የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡ በሀገር ውስጥ የተመረቱ በርካታ ውጤቶችን በመመልከቷ ኩራት እንደተሰማት የገለጸችው ተማሪ ዮሳን ዳንኤል፤ "ይህ ጉብኝት በቀጣይ በርትተን በመማር የተሻለ ስራ እንድንሰራ የሚያነሳሳን ነው" ስትል ተናግራለች። በዳይመንድ አካዳሚ የማህበራዊ ሳይንስ ዘርፍ ኃላፊ መምህር ፋንታ ጌታው በበኩላቸው፤ ኤክስፖው ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሪን ለማዳን እየተከናወነ ያለውን ስራ የሚያሳይ በመሆኑ የሚበረታታ ነው ብለዋል። ተማሪዎች ይህንን መመልከታቸው የነገ አገር ተረካቢ እንደመሆናቸው መጠን፣ ራሳቸውን ለተሻለ ስራ እንዲያዘጋጁ ትልቅ ግብዓት እንደሚሆናቸው አስረድተዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡሉልታ እንደገለጹት፤ ወጣቶች ኤክስፖውን መጎብኘታቸው በሀገር ውስጥ የሚመረቱ ምርቶችን አውቀው እንዲጠቀሙና የኢንዱስትሪ ባህል እንዲገነቡ ያስችላል። "የዛሬ ተማሪዎች የነገዋ የአገር ተረካቢዎች በመሆናቸው፣ የነገ ተልእኳቸውን ከኢንዱስትሪው ዘርፍ ጋር እያስተሳሰሩ እንዲሄዱ ያግዛቸዋል" ሲሉ ሚኒስትር ዴኤታው አክለዋል።
የምስራቋ ፈርጥ ሐረር
May 8, 2026 69
የምስራቋ ፈርጥ ሐረር ከተማ የትላንት ከፍታዋን በሚመጥን ደረጃ በጀጎል ዓለም አቀፍ ቅርስን ጨምሮ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች ውጤታማ የኮሪደር ልማት ስራዎች ተከናውነዋል። የኮሪደር ልማት ስራዎቹም ትላንትን ከዛሬ የሚያስተሳስሩ ነገንም ታሳቢ ያደረጉ ናቸው። የገናና ስልጣኔ መነሻ ሐረር በየቀኑ ገናናነቷንና እድሜዋን በሚመጥን ደረጃ ከፍታዋን እያረጋገጠች ትገኛለች። በከተማው የተሰሩና እየተሰሩ የሚገኙ የኮሪደር ልማት ስራዎች ለሌሎች የቅርስ ከተሞችም ተሞክሮ በሚሆን ደረጃ የቀደምት አባቶችን አሻራ ሳያደበዝዙ ይልቁንም ተጠብቆ እንዲቆይ በሚያስችልና ተጨማሪ ውበት በሚሆን መልኩ እውን ማድረግ ተችሏል። በየእለቱ እየፈካች የምትገኘው ሀረር ከተማ ዛሬ ላይ ለመጎብኘት የምታጓጓ ለመኖር የምትመረጥ ለነዋሪዎቿም የተመቸች ከተማ ሆናለች። ታሪካዊቷ ሀረር ከተማ ዛሬም አዳዲስ ታሪክ እየሰራች ትገኛለች።
ኤክስፖው ምርቶቻችንን ለማስተዋወቅና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ትልቅ ዕድል ፈጥሮልናል
May 8, 2026 77
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ)፦አራተኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶቻቸውን ለማስተዋወቅና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ትልቅ ዕድል እንደፈጠረላቸው አምራች ኢንዱስትሪዎች ገለጹ። "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሐሳብ ሲካሄድ የቆየው የ4ኛው "ኢትዮጵያ ታምርት" ኤክስፖ የማጠቃለያ መርሃ ግብር እየተካሄደ ነው፡፡ ኤክስፖው በከፍተኛ የመንግስት ስራ ኃላፊዎች፣ በሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ አባላት፣ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ በተማሪዎች እንዲሁም በመዲናዋ ነዋሪዎች ዘንድ በስፋት ተጎብኝቷል። ኢዜአ ያነጋገራቸው በኤክስፖው የተሳተፉ አምራች ኢንዱስትሪዎች፤ መድረኩ የተሻለ የገበያ ዕድልና የምርት ትስስር እንዳመጣላቸው ገልጸዋል። የኢ.ዜድ.ኤም ትሬዲንግ ኢንቨስትመንት የማርኬቲንግ ባለሙያ አቶ ቢኒያም ተስፋዬ፤ ድርጅታቸው በፕላስቲክ ፓይፕ ምርት ተሰማርቶ ቀደም ሲል ከውጭ ይገቡ የነበሩ ምርቶችን መተካት መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ ኤክስፖው የሀገር ውስጥ ምርትን በማበረታታት ረገድ ትልቅ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል። የዳግም ኬኔዲ ማሽነሪዎች ማምረቻ ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ ግርማዬ ወልደገብርኤል በበኩላቸው፤ ፋብሪካቸው ከትራንስፎርመር ጀምሮ የተለያዩ የግብርና መሣሪያዎችን በማምረት ለሀገሪቱ የግብርና ትራንስፎርሜሽን የላቀ ጠቀሜታ እየሰጠ መሆኑን ጠቁመዋል። ኤክስፖው ኢትዮጵያ ማምረት እንደምትችል በተግባር ያሳየችበትና ለአምራቾች የሚፈለገውን ግብዓት በቀላሉ ለማግኘት የረዳቸው መሆኑንም ገልጸዋል። የሆራይዘን አዲስ ጎማ ማኑፋክቸሪንግ የደንበኞች አገልግሎት ኃላፊ አቶ ጌቱ አብዲሳ፤ ድርጅታቸው ለተለያዩ ተሽከርካሪዎች የሚሆኑ ጎማዎችን በሀገር ውስጥ በማምረት ከውጭ ጥገኝነት ለመላቀቅ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ድርጅቱ ከ800 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩንም አክለዋል። በኤክስፖው ላይ የተገኙ ሸማቾች በበኩላቸው፤ የተመለከቷቸው የሀገር ውስጥ ምርቶች የ"ይቻላል" መንፈስን ያሳዩ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የሚፈልጓቸውን ምርቶች ከአምራቾች በቀጥታና በተመጣጣኝ ዋጋ ለማግኘት መቻላቸውን ተናግረዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡሉልታ በበኩላቸው፤ በኤክስፖው ላይ ከ300 በላይ ኢንተርፕራይዞች መሳተፋቸውን ገልጸዋል። ኤክስፖው አምራቾች ምርታቸውን እንዲያስተዋውቁ፣ የልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉና ጠንካራ የገበያ ትስስር እንዲፈጥሩ ትልቅ ሚና መጫወቱን አብራርተዋል። መንግስት ኢትዮጵያን የአምራች ኢንዱስትሪ ማዕከል በማድረግ የአፍሪካ ተምሳሌት ለማድረግ ለሚሰራው ስራ ይህ ኤክስፖ ትልቅ ፋይዳ እንዳለውም ተናግረዋል፡፡ ሸማቾችም ምርቶችን በቀጥታ በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ዕድል የፈጠረ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው የአርሶ አደሩን የግብርና ምርታማነት ለማሳደግ እየሰራ ነው
May 8, 2026 176
ሮቤ፤ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ)፦የአርሶ አደሩን የግብርና ምርታማነት ለማሳደግና ለዘርፉ ተግዳሮቶች በጥናት መፍትሄ ለመስጠት በቅንጅት እየሰራ መሆኑን የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ገለጸ። ዩኒቨርሲቲው ከአርሶ አደሮች የምርምር ኮንፈረንስ ጎን ለጎን የግብርና ምርቶች እና የቴክኖሎጂ ግብዓቶችን ለማስተዋወቅ ያዘጋጀው አውደ ርዕይ ተከፍቷል። አውደ ርዕዩን መርቀው የከፈቱት የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ብርሃነመስቀል ጠና (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ዩኒቨርሲቲው ችግር ፈቺ የምርምር ውጤቶችን እና የማህበረሰብ አገልግሎቶችን ተደራሽ ማድረግን ግብ አድርጓ እየሰራ ነው። ለዚህም የአርሶ አደሮችን ሀገር በቀል እውቀት በምርምር በማስደገፍ የአርሶ አደሩን ምርታማነትና ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ከአውደርዕዩ ጎን ለጎን አርሶ አደሮች የተሳተፉበት የምርምር ኮንፈረንስ መካሄዱን የጠቀሱት ፕሬዚዳንቱ፣ ይህም የዩኒቨርሲቲው ተመራማሪዎችና የዘርፉ ባለድርሻዎች በአርሶ አደሩ ሀገር በቀል እውቀት ላይ ለምርምር የሚሆን መነሻ ግብአት እንዲያገኙ ያግዛቸዋል ብለዋል። የአርሶ አደሩን ችግር መሰረት ያላደረገ የምርምር ሥራ የተሟላ እንደማይሆን ገልጸው፣ አውደ ርዕዩና ኮንፈረንሱ በሁለቱ ወገኖች መካከል ያለውን ግንኙነት ያጠናክራል ብለዋል። ዩኒቨርሲቲው በምርምር የተደገፈ ግብርናን ለማስፋፋት ለአካባቢው ማህበረሰብ ዘርፈ-ብዙ ድጋፎችን በማድረግ የጀመረውን ጥረት አጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉም ፕሬዝዳንቱ አክለዋል። የኦሮሚያ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ በሪሶ ፈይሳ በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው ያዘጋጀው በአይነቱ ልዩ የሆነው የአርሶ አደሮች የምርምር ኮንፈረንስና የልምድ ልውውጥ መድረክ ለክልሉ ግብርና ዕድገት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ በተከፈተው አውደ ርዕይ የአርሶ አደሮች የተለያዩ የግብርና ምርቶች፣ በሰብል ላይ የሚከሰቱ የተለያዩ በሽታዎች ፎቶ ግራፍና መከላከያ መድሀኒቶችን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ የግብርና አጋዥ ቴክኖሎጂዎችም በአውደ ርዕዩ ላይ ለእይታ መቅረባቸው ታውቋል።
የህዝብን ተጠቃሚነት ለሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች የተሰጠው ትኩረት ተጠናክሮ ይቀጥላል
May 8, 2026 98
ጅማ፤ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ)፦ የህዝብን ተጠቃሚነት ለሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ግንባታ የተሰጠው ትኩረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሀላፊ ነመራ ቡሊ ገለጹ። በጅማ ከተማ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል። በምረቃ ስነ-ስርአቱ ላይ የተገኙት በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሀላፊ አቶ ነመራ ቡሊ፤ በክልሉ ዘላቂ ኢኮኖሚ ለመገንባት ግብ ተጥሎ እየተሰራ ነው። ለዚህም የህዝብን ተጠቃሚነት ለሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ግንባታ ትኩረት መሰጠቱን ጠቁመው ተግባሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። ባለፉት ጥቂት አመታት ሰፊ የስራ ዕድልን በመፍጠር የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተሰራው ስራ በርካታ ውጤቶች የተመዘገቡበት መሆኑን ጠቅሰዋል። በጅማ ከተማ የተመረቁት ፕሮጀክቶችም የዚሁ አካል ናቸው ብለዋል። የጅማ ከተማ ከንቲባ ጠሀ ቀመር በበኩላቸው፤ የብልፅግና ጉዟችንን እያረጋገጥን እንቀጥላለን ብለዋል። ከለውጡ በኋላ እየተገነቡ ያሉ ፕሮጀክቶች ብዛት ብቻ ሳይሆን ጥራት እና ፍጥነትንም ያማከሉ ናቸው ያሉት አቶ ጠሀ የያዝናቸውን ኢኒሼቲቮች ለማሳካት ሁሌም በቁርጠኝነት እንሰራለን ብለዋል። በከተማው በዚህ አመት ከ12 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶች እየተገነቡ መሆኑን አመልክተዋል። በከተማው በዛሬው እለት የማምረቻ ሼዶች ፣ የዶሮ እርባታ እና የገበያ ማዕከል እንዲሁም የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት ተመርቋል።
በክልሉ ለሚገኙ ኢንተርፕራይዞች የሀገር ውስጥና የውጭ ገበያ ትስስር ለመፍጠር ትኩረት ተደርጓል
May 8, 2026 97
ባህርዳር፤ ሚያዝያ 30/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ተደራጅተው በማምረት ላይ ለሚገኙ ኢንተርፕራይዞች የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር ገበያ ትስስር በመፍጠር ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በትኩረት እየሰራ መሆኑን የክልሉ ስራና ስልጠና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የገበያ ልማትና ግብይት ዳይሬክተር ፍቅረማርያም የኔአባት እንደገለጹት ቢሮው ወጣቶችን በማደራጀት ወደ ስራ በማስገባትና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል። በዚህም ተደራጅተው በማምረት ላይ ለሚገኙ 35ሺህ 287 ኢንተርፕራይዞች በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የገበያ ትስስር በመፍጠር ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። በተፈጠረው የገበያ ትስስርም ከ7 ቢሊየን ብር በላይ የሚገመት ግብይት መፈጸሙን ጠቁመው ትስስሩ የተፈጠረው ከተቋማት፣ ከኩባንያዎች፣ ከኢንተርፕራይዝ ለኢንተርፕራይዝና ከሌሎች ጋር ነው ብለዋል። በሀገር ውስጥ የተፈጠረው ትስስር በኮንስትራክሽን፣ በከተማ ግብርና፣ በማምረቻውና በአገልግሎት ዘርፎች ሲሆን በውጭ ሀገራት ደግሞ ኦፓል፣ ወርቅ፣ የባህላዊ አልባሳት፣ የባልትና ውጤቶችና ሌሎች ምርቶችን በመላክ መሆኑን ጠቅሰዋል። በቀሪ ወራትም የተጀመረውን የገበያ ትስስር በማጠናከር አዳዲስ ለገበያ የሚሆኑ ሀገራትን በማፈላለግ የኢንተርፕራይዞችን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በደሴ ከተማ ያሬድና ጓደኞቹ ሚስማር ማምረትና ማከፋፋል ማህበር አስተባባሪ ወጣት ሰለሞን ሞላ እንደገለጸው ሚስማር በማምረት ስራ ተደራጅተው ወደ ስራ በመግባት ተጠቃሚ መሆን ችለዋል። ምርታቸውንም በተመቻቸላቸው የገበያ ትስስር በደሴ ከተማና አካባቢው በማከፋፈል የተሻለ ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን ተናግሯል። በ2017 በጀት ዓመት ለ40ሺህ 117 ኢንተርፕራይዞች ከ7 ነጥብ 5 ቢሊየን በላይ ዋጋ ያላቸው የተለያዩ ምርቶች በውጭና በሀገር ውስጥ ገበያ ትስስር መፍጠር መቻሉንም ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በዞኑ በመጪው ክረምት የሚተከሉ የተሻሻሉ የቡና ችግኞች ተዘጋጅተዋል
May 8, 2026 100
ጭሮ፤ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ)፡-በምዕራብ ሐረርጌ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ከ37 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞች መዘጋጀታቸውን የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ፅህፈት ቤት ገለፀ። በጽህፈት ቤቱ የቡና እና ቅመማ ቅመም ልማት አስተባባሪ አቶ ኦሉማ በዳኔ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በመጪው ክረምት በዞኑ 13 ወረዳዎች የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል። የቡና ዝርያዎቹ አብዛኛውን ከመቻራ ግብርና ምርምር ማዕከል የተለቀቁ እና በሽታንና ድርቅን በመቋቋም በሄክታር እስከ 17 ኩንታል ምርት የመስጠት አቅም ያላቸው መሆናቸውን ነው የተናገሩት። በዞኑ የቡና ልማትን ለማስፋፋት እየተሰራ ሲሆን የአካባቢው አርሶ አደሮችም በክረምቱ ወቅት ለሚካሄደው የችግኝ ተከላ ጉድጓዶችን ማዘጋጀታቸውን አብራርተዋል። በዞኑ እስካሁን ከ129 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቡና ተክል መሸፈኑን አመልክተው በዘንድሮው ዓመት ለተከላ የተዘጋጀው የቡና ችግኝም ከዓምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በ8 ሚሊዮን ብልጫ እንዳለው አስታውቀዋል። በሚካሄደው የቡና ልማት ስራ ከ232 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ተሳታፊና ተጠቃሚ መሆናቸውን አብራርተዋል። የቦኬ ወረዳ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ፅህፈት ቤት የቡናና ቅመማ ቅመም ልማት አስተባባሪ አቶ ኢብራሂም ሐሰን በበኩላቸው በወረዳው በዚህ ዓመት 3 ሺህ ሄክታር አዲስ መሬት በቡና ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ከቡና ዝርያዎቹ መካከል ቡልቱም የተሰኘውና ከመቻራ ግብርና ምርምር ማእከል የወጣው የቡና ችግኝ በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል። በቦኬ ወረዳ ቦኬ ጥቃ ቀበሌ አርሶ አደር አይሻ መሐመድ እንዳሉት ለቡና ችግኝ ጥበቃና እንክብካቤ በማድረግ የስራ ዕድል በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልፀዋል። ከዚህ ባለፈም የጫት ምርት ያመርቱበት የነበረውን ሁለት ጥማድ መሬት የቡና ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን ነው የገለጹት ። ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ በቡና ልማት በመሳተፍ ተጠቃሚ ለመሆን መቻላቸውን የተናገሩት ደግሞ የቀበሌው አርሶ አደር ሞሚና ኢብራሂም ናቸው። በመጪው ክረምትም ከ500 በላይ ተጨማሪ የቡና ችግኞችን ለመትከል ጉድጓዶችን ማዘጋጀታቸውን ነው የተናገሩት።
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን አሳድጎታል
May 8, 2026 157
አርባ ምንጭ ፤ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ) ፡-የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን በማሳደግ ትርጉም ባለው መልኩ ህይወታችንን ቀይሮታል ሲሉ በጋሞ ዞን የመርሃ ግብሩ ተሳታፊዎች ገለጹ፡፡ የመርሃ ግብሩ ተሳታፊዎች ለኢዜአ እንደገለፁት፤ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር አመጋገባቸውን ከመቀየሩ ባሻገር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን አልቆታል። በዚህም መርሃ ግብሩ ህይወታቸውን ትርጉም ባለው መንገድ እንደቀየረም ተሳታፊዎቹ አፅንኦት ሰጥተዋል። በዞኑ በምዕራብ አባያ ወረዳ አንኮበር ቀበሌ "የጦይሎ ንብ አንቢዎች ማህበር ሰብሳቢ ደሰ ኡታሎ፤ የማህበሩ አባላት በንብ ማነብ ስራ ላይ በመሰማራት ከማር ሽያጭ ጥሪት እንዲያፈሩ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። አባላቱ በሚያገኙት ገቢ ከመኖሪያ ቤት ግንባታ ጀምሮ የቤት ቁሳቁሶችን በማሟላትና ልጆቻቸውን በማስተማር ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ እንደሚገኙ ነው የተናገሩት። መንግስት ባመቻቸላቸው 19 ሄክታር ደን ውስጥ የንብ ማነብ ተግባራትን ከማከናወን ጎን ለጎን የደን ጥበቃ ስራ እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። ማህበሩ በ102 ዘመናዊና በ2 ሺህ 530 ባህላዊ ቀፎዎች ማር በማምረት በየዓመቱ ከ100 ሺህ ብር በላይ እየቆጠቡ ይገኛሉ። በቦረዳ ወረዳ መሳ ቡንታዛ ቀበሌ የአንድነት የዶሮ አርቢ ማህበር ሰብሳቢ ወጣት መስፍን ደነቀ በበኩላቸው፤ በመርሃ ግብሩ ያረቧቸውን ዶሮዎች ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። መርሃ ግብሩ የወረዳው ነዋሪዎች የምግብ ዋስትናቸውን እንዲያረጋግጡ እያገዘ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የቦረዳ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ደጉ ማጃ ናቸው። መርሃ ግብሩ በህብረተሰቡ መካከል መልካም የሆነ መነቃቃትና የስራ ባህልን በመፍጠር ከድህነት እንዲላቀቁ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ብለዋል። የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ወርቅነህ ካልሳ በበኩላቸው፤ የሌማት ትሩፋት ኢንሼቲቭ በዞኑ በ14 ወረዳዎችና በ6 ከተማ አስተዳደሮች እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በሁሉም መዋቅሮች የወተት፣ የስጋ፣ የዶሮ፣ የማር እና የዓሣ መንደሮች የተደራጁ ሲሆን በዝርያ ማሻሻልና በጤና አገልግሎት የተቀናጀ ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።
የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም ለዚምባቡዌ ባለሃብቶች የንግድና ኢንቨስትመንት ተሳትፎ መነቃቃት እየፈጠረ ነው
May 8, 2026 234
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም ለዚምባቡዌ ባለሃብቶች የንግድና ኢንቨስትመንት ተሳትፎ መነቃቃት እየፈጠረ መሆኑን በዚምባቡዌ፣ በዛምቢያና በሞሪሽየስ የኢትዮጵያ ባለ ሙሉ ስልጣን አምባሳደር እና የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ የጋራ ገበያ(ኮሜሳ) የኢትዮጵያ ቋሚ ተጠሪ ረሽድ መሀመድ ገለጹ። የኢትዮጵያና ዚምባቡዌን ዲፕሎማሲያዊ ትብብር በማጠናከር በኢኮኖሚ ግንኙነት ዘርፍ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑንም ተናግረዋል። ኢትዮጵያና ዚምባቡዌ በፖለቲካና በፓን-አፍሪካኒዝም ዕሳቤ የተመሠረተ ጠንካራና ታሪካዊ የዲፕሎማሲ ወዳጅነት ያላቸው ሀገራት ናቸው። የቀድሞዋ ደቡብ ሮዴዢያ የአሁኗ ዚምባቡዌ እ.አ.አ ከ1960ዎቹ እስከ 1980 ድረስ ከብሪታኒያ ቅኝ አገዛዝ ነጻ ለመውጣት ባደረገችው እልህ አስጨራሽ የነፃነት ተጋድሎ የኢትዮጵያ ድጋፍ በታሪክ ይወሳል። የዚምባቡዌ የነፃነት ተጋድሎና የኢትዮጵያ ድጋፍም በታሪክ ውስጥ በደማቅ ቀለም የተፃፈ የአፍሪካውያን አህጉራዊ አንድነት መገለጫ ተደርጎ ይወሰዳል። ኢትዮጵያም በዚምባቡዊ የነፃነት ተጋድሎ ዘመንም የቅኝ አገዛዝ ስርዓትን በፓን-አፍሪካኒዝም ዕሳቤን የማይተካ የገንዘብና ወታደራዊ ስልጠና ድጋፍ በመስጠት ግንባር ቀደም ሚና ተወጥታለች። የሀገራቱ የሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ መድረክ የአህጉሪቱን ጥቅምና ፍላጎት የሚያስጠብቁ የጋራ አቋሞችን በዓለም አደባባይ በማንፀባረቅ የሚተባበሩ ጠንካራ ወዳጅ ሀገራት ለመሆን በቅተዋል። በአሁኑ ወቅትም ሀገራቱ በግብርና፣ ቱሪዝም፣ በአቪዬሽን ዘርፍና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በደምና በጋራ ነፃነት የተመሰረተ አጋርነታቸውን እያስቀጠሉ ይገኛሉ። አምባሳደር ረሽድ መሐመድ በቨርቿል ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኢትዮ-ዚምባቡዌ ግንኙነት በቅኝ ግዛት ዘመን የነፃነት ተጋድሎ ወቅት የተጀመረና በታሪካዊ ወዳጅነት የተመሠረተ ነው። ለአብነትም ዚምባቡዌ የቅኝ ግዛት ነፃነቷን በተቀዳጀች ማግስት እ.አ.አ በ1980ዎቹ ሀገራቱ በሀራሬና አዲስ አበባ ኤምባሲዎቻቸውን በመክፈት ይፋዊ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጀመራቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም የሀገራቱ ታሪካዊ የሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነት በተለያዩ የኢኮኖሚ መስኮች እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በዚህም በቅርቡ የኢትዮጵያውያን የቆዳ ውጤቶች አምራች ኢንዱስትሪዎች በዚምባቡዌ ዓለምአቀፍ የንግድ ትርዒት በመሳተፍ የንግድ ምርታቸውን በማስዋወቅ የንግድ ትስስር መፍጠር እንደቻሉ አንስተዋል። የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ማሻሻያ አስቻይ የልማት ምኅዳር ለዚምባቡዌ አልሚ ባለሃብቶች በማስተዋወቅ የተከናወኑ ተግባራትም በንግድና ኢንቨስትመንት ተሳትፎ መነቃቃት እየፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ስምምነትን መፈረሟና የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) አባል መሆኗ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል። በዚምባቡዌ ዓለምአቀፍ የንግድ ትርዒት የተሳተፉ ኢትዮጵያውያን አምራቾችን የጉዞና አገልግሎት ወጪ በምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) እንዲሸፈን መደረጉንም ገልጸዋል። በምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) የዳኞች ሹመትም ኢትዮጵያ በኮሜሳ የፍትሕ ፍርድ ቤት የሚገባትን ውክልና ማግኘቷን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድም በሶስት የዚምባቡዌ ከተሞች በሳምንት 23 በረራዎችን በማድረግ የሀገራቱን የንግድና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት እያጎለበተ እንደሚገኝ አንስተዋል።
በአርብቶ አደሩ አካባቢ የእንስሳት ኢንሹራንስ ሽፋንን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
May 8, 2026 72
አዳማ፤ ሚያዝያ 30/2018(ኢዜአ)፡- በአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ አካባቢ የእንስሳት ኢንሹራንስ ሽፋንን በማሳደግ የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቀነስ ትኩረት መሰጠቱን የኦሮሚያ መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ገለፀ። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ሮባ ቱርጬ ለኢዜአ እንደገለጹት፤በክልሉ የአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ የእንስሳት ሀብት የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቀነስ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥርዓትን የማጠናከር ስራ እየተሰራ ይገኛል። በተጨማሪም ፣የመኖ እቅርቦትና የውሃ አማራጮችን ማስፋት፣የእንስሳት ቁጥርን የማመጣጠን እና የክትባት አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ነው የገለጹት ። የእንስሳት እንሹራንስ ሽፋንን ተደራሽ በማድረግም በድርቅ ወቅት ለመኖ ፣ የውሃ አቅርቦት፣ ለእንስሳት መድሀኒትና ለጤና አገልግሎት እንዲያውል እየተሰራ ነው ብለዋል። በዚህም 130 ሺህ በላይ አርብቶ አደሮች የኢንሹራንስ አባል መሆናቸውን የገለጹት ምክትል የቢሮ ኃላፊው ይህም የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት በተጨባጭ ማረጋገጥ ያስቻለ መሆኑን ጠቁመዋል። ለአብነትም የኢንሹራንሱ አባል ለሆኑ አርብቶ አደሮች ለመኖ እና ውሃ አቅርቦት፤ ለእንስሳት ጤና መጠበቂያ የሚሆን ከ930 ሚሊዮን ብር በላይ ኢንሹራንስ መከፈሉንም ጠቅሰዋል። በቀጣይም ድርቅን በዘላቂነት ለመቋቋምና አርብቶ አደሩ ከእንስሳት ሀብቱ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ የኢንሹራንስ ሽፋኑ ተደራሽነት ለማስፋት ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየሰራን ነው ብለዋል።
በኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ እየታየ ያለው ለውጥ ለአፍሪካ አርአያ የሚሆን ነው
May 8, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ እየታየ ያለው ለውጥ ለአፍሪካ አርአያ የሚሆን ነው ሲሉ በመጀመሪያው የአፍሪካ ማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ጉባኤ ተሣታፊዎች ገለጹ፡፡ የመጀመሪያው የአፍሪካ ማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ጉባኤ (ASMIS 2026) "ተፅዕኖ ፈጣሪዎች ለተሻለች አፍሪካ" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ ዓድዋ ድል መታሰቢያ በደመቀ ሁኔታ እየተካሄደ ይገኛል። ፐልስ ኦፍ አፍሪካ /pulse of Africa/ ከኤ.ጂ.ኤ የቴክኖሎጂ ኢንተርፕራይዝ ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ጉባኤ ነው፡፡ የጉባኤው ተሳታፊዎች የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት፣ በአዲስ አበባ የተገነቡ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን እና የኮሪደር ልማቶችን እንዲሁም ልዩ ልዩ የልማት ስራዎችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል፡፡ በዚሁ ወቅት ታዋቂው ጋናዊ የይዘት ፈጣሪ በርትሆልድ ኮቢ ዊንክለር (ዎዴ ማያ) በኢትዮጵያ እየታየ ያለው ሁለንተናዊ ለውጥ ለመላው አፍሪካ አህጉር ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን ተናግሯል። በኢትዮጵያ ካለው ጥልቅ ፍቅር የተነሳ በሀገሪቱ የታየውን ለውጥ ለዓለም ለማሳየት በድጋሚ መምጣቱን ጠቅሶ እ.ኤ.አ በ2017 ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ከነበረበት ወቅት ጋር ሲነፃፀር አሁን በ2025 እና 2026 እያያት ያለችው ኢትዮጵያ በአዲስ ገጽታና ምዕራፍ ላይ እንደምትገኝ መስክሯል፡፡ በተለይም በሀገሪቱ እየተገነቡ ያሉ ሰፋፊ መንገዶች፣ ግዙፍ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እና አዲሱ አውሮፕላን ማረፊያ ለሀገሪቱ ዕድገት ማሳያና እጅግ የሚደነቁ ተግባራት መሆናቸውን ጠቅሷል፡፡ ይህ ስኬት ለአህጉሪቱ ብልጽግና ተስፋ የሚሰጥ በመሆኑ መላው አፍሪካ ከኢትዮጵያ ተሞክሮ ሊቀስም ይገባል ብሏል። ከናይጄሪያ የመጣው የይዘት ፈጣሪ ኦዲናካ በበኩሉ፣ ኢትዮጵያ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ልማት ቀዳሚ መሆኗን መመልከቱን ተናግሯል፡፡ ቴክኖሎጂው ዓለምን እየተቆጣጠረ ባለበት በዚህ ወቅት ሀገሪቱ ለዘርፉ የሰጠችው ትኩረት የሚደነቅ መሆኑን ገልጿል። ይህ በሰው ሰራሽ አስተውሎት የታየው ስኬት ግለሰቦችንም ሆነ ሀገርን ለማልማት ያለው ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑን ገልጾ የኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ ጉዞ የሚደነቅ ነው ብሏል፡፡ ከሌሴቶ የመጣው የይዘት ፈጣሪ ቴኤሎ ሉዓሎ እንዳለውም፤ ኢትዮጵያ በቅኝ ግዛት አለመገዛቷና የራሷ የሆነ የቀን መቁጠሪያ ባለቤት መሆኗ ለአፍሪካውያን ታላቅ ኩራትና የማንነት መገለጫ መሆኑን ተናግሯል። የታየው የሀገሪቱ የበለፀገ ታሪክና ጠንካራ ባህል ሌሎች ሀገራትም የራሳቸውን ቱባ ባህል ጠብቀው እንዲቆዩ ትምህርት የሚሰጥ ነው ሲል ገልጿል፡፡
በደቡብ ወሎ ዞን የመጠጥ ውሃ አቅርቦትና ተደራሽነት እያደገ ነው
May 8, 2026 135
ደሴ፤ ሚያዚያ 30/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ወሎ ዞን የመጠጥ ውሃ አቅርቦትና ተደራሽነት እያደገ መሆኑን የዞኑ ውሃና ኢነርጂ መምሪያ ገለጸ። በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት በዞኑ 331 አነስተኛ የውሃ ልማት ፕሮጀክቶች እና 5 ጥልቅ የውሃ ጉድጓዶች ለአገልገሎት መብቃታቸው ታውቋል። በዚህም የመጠጥ ውሃ አቅርቦትና ተደራሽነት እያደገ መሆኑን የዞኑ ውሃና ኢነርጂ መምሪያ ኃላፊ አቶ ጌታቸው ጽጌ ገልጸዋል። የፕሮጀክቶቹ ግንባታ በመንግስት ጥረት፣ በህብረተሰቡና በአጋር አካላት ትብብር የተከናወነ መሆኑን አንስተው፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ ተደራሽነትን ለማስፋት በተደረገው እንቅስቃሴ ከ149 ሺህ 964 በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። በግንባታ ላይ የሚገኙ ሌሎች 138 አነስተኛ የውሃ ልማት ፕሮጀክቶች መኖራቸውን የጠቆሙት ኃላፊው፣ በቀሪ ወራት ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የዞኑ ነዋሪዎች ወይዘሮ ሀዋ ፋሪስ እና አቶ ሰይድ መሃመድ በሰጡት አስተያየት ከዚህ በፊት የመጠጥ ውሃ ፍለጋ ብዙ እንግልትና ወጪ ይገጥማቸው እንደነበር አንስተው፣ በመንግስት ጥረትና በህብረተሰቡ ትብብር በተሰራው ሥራ በአቅራቢያችን ውሃ ማግኘት ችለናል፤ ለዚህም እናመሰግናለን ብለዋል። በደቡብ ወሎ ዞን ባለፈው በጀት ዓመት ከ181 ሺህ በላይ ነዋሪዎችን የንጹህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ከዞኑ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በምዕራብ ሸዋ እና ሐረርጌ ዞኖች በበጋ ስንዴ ከለማው ማሳ ከ9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተሰበሰበ
May 8, 2026 80
አምቦ/ጭሮ፤ ሚያዝያ 30/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ እና ሐረርጌ ዞኖች በዘንድሮ ዓመት የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከ9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የየዞኖቹ ግብርና ጽህፈት ቤቶች አስታወቁ። በምዕራብ ሸዋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት የመስኖ ልማት ባለሙያ ቢቂላ ጉቱ ለኢዜአ እንዳሉት፤ አርሶ አደሩ በምግብ ራሱን ለማስቻል ለበጋ መስኖ ልማት ስራ ትኩረት ተሰጥቷል። በዞኑ በዘንድሮ የበጋ ወቅት 388 ሺህ ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴን በማልማት ከ16 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱንም ነው የገለጹት። በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩ ቀድሞ የደረሰውን ሰብል እየሰበሰበ ሲሆን የሰው ኃይልና ሜካናይዜሽንን በማቀናጀት መከናወኑን ገልፀዋል። እስካሁን ባለው ሂደትም በበጋ መስኖ ስንዴ ከተሸፈነው 253 ሺህ ሄክታር ከሚሆን ማሳ ላይ 7 ነጥብ 9 ሚሊየን ኩንታል ምርት መሰብሰቡን አስታውቀዋል። ዘንድሮ የተሻለ ምርት መሰብሰቡን አመልክተው ለዚህም አርሶ አደሩ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችንና የግብርና ግብዓቶችን በአግባቡ እንዲጠቀም በመደረጉ ነው ብለዋል። ቀሪው የበጋ ስንዴ ምርትም ከብክነት በጸዳ መልኩ የመሰብሰቡ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በምዕራብ ሸዋ ዞን የወልመራ ወረዳ አርሶ አደር ብርሀኑ ተሾመ በበኩላቸው፤ በበጋ ስንዴ ልማት መሳተፍ ከጀመሩ ከአራት ዓመት ወዲህ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በዚህ ዓመት የመስኖ ውሃ በመጠቀም ካለሙት አንድ ሄክታር ማሳ 40 ኩንታል የስንዴ ምርት መሰብሰባቸውን ጠቁመዋል። በኩታ ገጠም ስነ-ዘዴ በዓመት ሁለት ጊዜ በማምረት የተሻለ ገቢ በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ አርሶ አደር ገላና ሰቦቃ ናቸው። በተመሳሳይም በክልሉ ምዕራብ ሐረርጌ ዞን በዘንድሮው የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከ1 ነጥብ 3 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ፅህፈት ቤት አስታወቋል። በጽህፈት ቤቱ የስንዴ ልማት አስተባባሪ አቶ ሀቢብ አብዱልከሪም እንዳስታወቁት፤ በዞኑ 15 ወረዳዎች በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት 50 ሺህ የሚጠጉ አርሶ አደሮች ተሳትፈው ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። የምርት ማሰባሰብ ሂደቱ በሜካናይዜሽን መታገዙን ጠቁመው በአሁኑ ወቅት ምርቱ ሙሉ በሙሉ ተሰብስቦ መግባቱን አስታውቀዋል።
በዞኑ በመኸር ወቅት ከ484 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ሰብል ለማልማት ዝግጅት እየተደረገ ነው
May 8, 2026 75
ጊምቢ፣ ሚያዝያ 30/2018 (ኢዜአ) ፡-በምእራብ ወለጋ ዞን በመኸር ወቅት ከ484 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የአዝዕርት ልማትና እጽዋት ጥበቃ ቡድን መሪ ወይዘሮ እጅጋየው አስፋው ለኢዜአ እንደገለጹት በዞኑ በ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት 484 ሺህ 76 ሄክታር መሬት አርሶ በተለያዩ ሰብሎች ዘር ለመሸፈን የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው ። የመኸር እርሻውን ውጤታማ ለማድረግ ለኩታ ገጠም እርሻና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። በምርት ወቅቱ በቆሎ፣ ገብስ፣ ቦሎቄ፣ ስንዴና ሌሎች ሰብሎች እንደሚለሙ ጠቁመው ለምርት ማሳደጊያ የሚሆን ምርጥ ዘር እና የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ ለአርሶ አደሩ እየቀረበ መሆኑን ተናግረዋል። በምርት ወቅቱ የተሻለ ምርት ለማግኘት በአሲድ የተጎዱ መሬቶችን በኖራ የማከም ስራ እየተከናወነ መሆኑንም አመልክተዋል። እንደ ቡድን መሪዋ ገለጻ በምርት ወቅቱ ከ16 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ ይጠበቃል። በመኸር አዝመራው የሚያስፈልጋቸውን ግብዓት በወቅቱ በማግኘታቸው መሬታቸውን ደጋግመው በማረስ ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የጊምቢ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ቱሉ አኩማ ናቸው። በአሲድ የተጠቃ መሬታቸውን በግብርና ባለሙያዎች ምክር በመታገዝ በኖራ በማከም ጭምር ለዘር ማዘጋጀታቸውን ተናግረዋል ። ሌላው የላሎ አሳቢ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር እንዳለ ቶላ፣ በበኩላቸው መሬታቸውን በኩታ ገጠም ማልማት ከጀመሩ ወዲህ የሚያገኙት ምርት እያደገ በመምጣቱ በዘንድሮ መኸርም ተግባሩን ማስቀጠላቸውን ገልጸዋል ። በመኸር ልማቱ ምርታማነታቸው የጨመሩ የበቆሎና ስንዴ ምርጥ ዘር በማግኘታቸው ስራቸውን ለማሳካት እየተጉ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በሸገር ከተማ በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ95ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይለማል
May 8, 2026 74
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 30/2018(ኢዜአ)፦ በሸገር ከተማ በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ95 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ወደ ስራ መገባቱን የከተማው ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በከተማ አስተዳደሩ የከተማ ግብርና ዕህፈት ቤት ሀላፊ ደጀኔ በቀለ ለኢዜአ እንደገለጹት በከተማው በመኸር እርሻ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከፍተኛ እንቅስቃሴ እየተደረገ ነው። የመኸር እርሻውን ውጤታማ ለማድረግ የስንዴ፣ ጤፍ፣ የገብስና ሌሎች ምርጥ ዘሮችንና ማዳበሪያን ለአርሶ አደሮች በወቅቱ የማድረስና የግብርና ባለሙያዎች ክትትልና ድጋፍ እየተደረገ ነው ብለዋል። በዘንድሮው የመኸር እርሻ 47ሺህ 751 አርሶ አደሮችን በማሳተፍ 95ሺህ 500 ሄክታር መሬት በማልማት 4 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለማግኘት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ጠቁመዋል። የመኸር እርሻ ልማቱን ለማሳካትም አሲዳማ መሬቶችን በኖራ የማከምና ለሜካናይዜሽን ትኩረት መሰጠቱን አንስተዋል። ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግም የግብርና ግብዓት አቅርቦት በዩኒየኖችና ማህበራት በኩል ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ ነው ብለዋል። የምርጥ ዘር አቅርቦትንም ለማሳደግ የዘር ብዜት ከሚያቀርቡ ተቋማት ጋር በመቀናጀት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። የአፈር ለምነትን ለመጨመርም የተፈጥሮ ማዳበሪያ መዘጋጀቱን ያነሱት ሀላፊው፣ አሲዳማ መሬት ለማከም ደግሞ ከ2ሺህ 400 ኩንታል በላይ ኖራ መቅረቡን ገልጸዋል።
በአዲስ አበባ የተመለከትናቸው ሁለንተናዊ የልማት ስኬቶች ለሌሎች የአፍሪካ ከተሞች ትልቅ ተምሳሌት የሚሆኑ ናቸው
May 7, 2026 201
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 29/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የተመለከትናቸው ሁለንተናዊ የልማት ስኬቶች ለሌሎች የአፍሪካ ከተሞች ትልቅ ተምሳሌት መሆናቸውን የአፍሪካ ማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ጉባኤ ተሳታፊዎች ገለጹ፡፡ የመጀመሪያው የአፍሪካ ማህበራዊ ሚዲያ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች ጉባኤ (ASMIS 2026) በአዲስ አበባ ዓድዋ ድል መታሰቢያ ዛሬ እና ነገ ይካሄዳል። በጉባኤው ለመታደም ከ30 የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ 321 ሚሊየን በላይ የማህበራዊ ሚዲያ ተከታዮች ያሏቸው 61 ተጽዕኖ ፈጣሪዎች በአዲስ አበባ ከትመዋል። በተጨማሪም 150 ሚሊየን ተከታዮች ያላቸው 120 ኢትዮጵያውያን የይዘት ፈጣሪዎች በጋራ በመሰባሰብ፣ የዓለም የዲፕሎማሲ ማዕከል በሆነችው አዲስ አበባ አዲስ የዲጂታል ታሪክ ለመጻፍ ተዘጋጅተዋል፡፡ ፐልስ ኦፍ አፍሪካ /pulse of Africa/ ከኤ.ጂ.ኤ የቴክኖሎጂ ኢንተርፕራይዝ ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ጉባዔ "ተፅዕኖ ፈጣሪዎች ለተሻለች አፍሪካ" የሚል መሪ ሀሳብ ይዟል። የጉባኤው ተሳታፊዎች የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት፣ በአዲስ አበባ የተገነቡ ግዙፍ ፕሮጀክቶችንና የኮሪደር ልማቶችን እንዲሁም ልዩ ልዩ የልማት ስራዎችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል፡፡ ኬንያዊው የጉብኝቱ ተሳታፊ በቴ ጆጉ በሰጠው አስተያየት፤ በአዲስ አበባ የተመለከታቸው ግዙፍ ፕሮጀክቶችና የኮሪደር ልማቶች ከተማዋን ለነዋሪዎች ምቹ ከማድረግ ባለፈ ገጽታዋን በእጅጉ መቀየራቸውን ገልጿል። የአዲስ አበባ የከተማ እድገት፣ የጎዳናዎች ስፋትና ውበት የሚያስደንቅ መሆኑን በአካል ማረጋገጡንም ተናግሯል። በኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት የተመለከተው የቴክኖሎጂ ትኩረትም ሀገሪቱ ለዘመናዊ አሰራር የሰጠችውን ግምት የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሷል። በከተማዋ የታዩት ሁለንተናዊ የልማት ስኬቶች ለሌሎች የአፍሪካ ከተሞች ትልቅ ተምሳሌት እንደሚሆኑም ገልጿል። ከቡርኪናፋሶ የመጣው ማህበራዊ ሚዲያ አንቂ ጃጓር ኢኮ እንዳለው፤ አዲስ አበባን በአካል በመጎብኘቱ መደሰቱን ገልጾ፣ ከተማዋ ሁሉም አፍሪካዊ ሊማርባት የሚገባ የልማት ማዕከል መሆኗን መመልከቱን ተናግሯል። በኢትዮጵያውያን እንግዳ ተቀባይነት መደሰቱን የገለጸው የማህበራዊ ሚዲያ አንቂው፣ ወደ ሀገሩ ሲመለስም የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆኖ እንደሚሰራ አረጋግጧል። የአዲስ አበባ ፈጣን እድገት ለአህጉሪቱ ትልቅ ተሞክሮ መሆኑንም ጨምሮ ጠቅሷል፡፡
የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ የሀገሪቱን መጻዒ እድል ብሩህ የሚያደርጉ የኢንዱስትሪ ውጤቶች የታዩበት ነው
May 7, 2026 163
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 29/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ የሀገሪቱን መጻዒ እድል ብሩህ የሚያደርጉ የኢንዱስትሪ ውጤቶች የታዩበት መሆኑን ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ ገለጹ። የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ አራተኛውን የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ኤክስፖ ጎብኝተዋል። ፕሬዝዳንቱ በጉብኝታቸው ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ በኤክስፖው የሀገሪቱን መጻዒ እድል ብሩህ የሚያደርጉ የኢንዱስትሪ ውጤቶች መመልከታቸውን ገልጸዋል። የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ የሀገር ውስጥ የማምረት አቅምን በማጠናከር፣ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን በማሳደግና የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማሳለጥ በኩል ተጨባጭ ውጤቶች የታዩበት መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ሉዓላዊነቷን የሚያረጋግጡ የኢንዱስትሪ ምርቶችን በስፋት እያመረተች መሆኑን ጠቁመው፤ ለዚህም የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ቆንፅላዎችና የዲፕሎማሲ ሚሲዮኖች የሀገር ውስጥ ምርቶችን በአምባሳደርነት የማስተዋወቅና ሰፊ የገበያ እድሎችን የመፍጠር ኃላፊነት እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። ኤክስፖው የሀገር በቀል ምርቶችን አቅም ለዓለም ከማሳየት ባለፈ፣ ኢትዮጵያ በኢንዱስትሪው ዘርፍ የጀመረችውን የብልጽግና ጉዞ የሚያሳይ እንደሆነ ተገልጿል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 25 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን አራተኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ መርቀው መክፈታቸው ይታወቃል።