ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የምግብ ሉዓላዊነት - ከተረጂነት መላቀቂያው መንገድ
Apr 20, 2026 22
በሙሴ መለሰ ኢትዮጵያ ከተረጂነትና ጠባቂነት መፋቻ መንገዶች መካከል የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ አንዱ ብልኀት አድርጋ እየታተረች ነው። ይህን ተከትሎም የዜጎችን የምግብ ፍላጎት በራስ የምርት ዐቅም የመሸፈን ሥራ በመከወን ከጠባቂነት ለመላቀቅ እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎች ስኬታማ ናቸው። ለዚህም ኢትዮጵያ በስንዴ ልማት ከልመና ወጥታ ወደ ውጭ ገበያ መላክ መጀመሯ አሥረጅ ነው። በመሆኑም ከውጭ የኢኮኖሚ ጥገኝነት በመላቀቅ የዜጎችን የምግብ ሉዓላዊነት ለማስከበር በስንዴ ልማት የተመዘገበውን ስኬት በሌሎች የግብርና ዘርፎች ለመድገም ርብርብ እየተደረገ ነው። በዚህም መሠረት በሩዝ፣ አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ ሻይ ቅጠል እና ሌሎች የተለያዩ ሰብሎች ላይ እየተከናወነ ያለው ሥራ አበረታች ውጤት እያስገኘ ነው። የተባበሩት መንግሥታት የምግብ እና የግብርና ድርጅት (ፋኦ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በምግብ ዋስትናና በተመጣጠነ የምግብ አቅርቦት ላሳዩት ርዕይ፣ የአመራር ቁርጠኝነት የአግሪኮላ ሜዳሊያ በ2016 ዓ.ም ማበርከቱ ለምግብ ሉዓላዊነት ጥረት የተሰጠ ዕውቅና ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ረሃብን ከማስቀረት ባለፈ የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ብሔራዊ ብልጽግናን ዕውን ለማድረግ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በርካታ ያልተነኩ ጥሬ ሃብቶች፣ተስማሚ የዓየር ንብረት፣ ለሥራ ትጉ የሆነ ወጣት እንዳላት እና እነዚህን ሃብቶች ታሳቢ በማድረግ የታሪክ ዐውራ የሆነችውን ሀገር ልማት ወደፊት ለማራመድ የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አስረድተዋል። በአንድ ወቅት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስከበር ዋጋ እንደከፈልን ሁሉ፤ ከምግብ ጥገኝነት ለመላቀቅ በትጋት መሥራት ይገባል ሲሉ ማስገንዘባቸው ይታወሳል። የምግብ ሉዓላዊነት፣የቴክኖሎጂ ሉዓላዊነት፣ የበጀት ሉዓላዊነት ታላቁን የሀገር ሉዓላዊነት በጽናት የሚያቆሙ መሆናቸውንም አብራርተዋል። እነዚህን የሉዓላዊነት ዘርፎች ለማስከበርም ብሔራዊ ዐርበኝነት እንደሚያስፈልግ አስረድተዋል። ሀገራዊ ትልሙ ኢትዮጵያን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለተሟላ ሀገራዊ ክብር፣ ነጻነት እና ሉዓላዊነት የሚያሸጋግር መልካም ጅማሮ ነው። #የምግብ_ሉዓላዊነት #ኢዜአ
ኢትዮጵያ እና እንግሊዝ በልማት እና በኢንቨስትመንት ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር ተስማሙ
Apr 20, 2026 30
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ እና እንግሊዝ በልማት እና በኢንቨስትመንት ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር ተስማምተዋል። በዋሺንግተን ዲሲ ሲካሔድ ከቆየው የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) እና የዓለም ባንክ ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብሰባ ጎን ለጎን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ከእንግሊዙ ዓለም አቀፍ ልማት ሚኒስትር ባሮኒስ ቻፕማን ጋር ተወያይተዋል። በውይይታቸውም በሁለቱ ሃገራት መካከል ያለውን የልማት የንግድ እና የኢንቨስትመንት ትብብርና አጋርነት ለማጠናከር ተስማምተዋል።   አቶ አህመድ ሽዴ በኢትዮጵያ ያለውን ጠንካራ የኢኮኖሚ ሪፎርም ሂደትና የተገኙ ስኬቶችን በተመለከተ ገለጻ አደርገዋል። ኢትዮጵያ ከእንግሊዝ ጋር ያላትን ጠንካራ አጋርነት ያነሱት ሚኒስትሩ የእንግሊዝ መንግስት የሚያደርገውን ድጋፍ አንዲያጠናክርም ጠይቀዋል። ባሮኒስ ቻፕማን በበኩላቸው ኢትዮጵያ እያካሔደች ያለውን የለውጥ ስራ በማድነቅ የእንግሊዝ መንግስት የልማት አጋርነቱን ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኑን ገልጸዋል። ሚኒስትሯ አያይዘውም ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ሰላምና መረጋጋት ዙሪያ ያላትን ቁልፍ ሚና አንስተዋል። ሁለቱ ወገኖች በውይይታቸው የሃገራቱን አጋርነት ከማስፋት ባለፈ በንግድ ፣ በልማትና በኢንቨስትመንት እንዲሁም በኢኮኖሚ ትብብራቸውን ለማጠናከር ተስማምተዋል።
መንግሥት የጠራ ፖሊሲ ሲኖረው ፍሬያማ ሥራ ሊሠራ እንደሚችል የተጀመሩ እንቅስቃሴዎች ያሳያሉ
Apr 19, 2026 589
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- መንግሥት የጠራ ፖሊሲ ሲኖረውና ማስፈጸሚያ ስትራቴጂው ያን ለመመገብ የሚያስችል ሲሆን ምን ዓይነት ፍሬያማ ሥራ ሊሠራ እንደሚችል የተጀመሩ አጠቃላይ እንቅስቃሴዎች ያመላክታሉ ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ የሐሮ ደንዲ ሎጅን የመረቁ ሲሆን፤ ከምረቃው በኋላም ማብራሪያ ሰጥተዋል።   በማብራሪያቸውም፤መንግሥት የጠራ ፖሊሲ ሲኖረው፣ ማስፈጸሚያ ስትራቴጂው ያን ለመመገብ የሚያስችል ሲሆን እና የማስፈጸም ዐቅም በተቋም ደረጃ እየገነባ ሲሄድ ምን ዓይነት ፍሬያማ ሥራ ሊሠራ እንደሚችል ኢትዮጵያ ውስጥ የተጀመሩ አጠቃላይ እንቅስቃሴዎች ያመላክታሉ ብለዋል። እንደ ሀገር አምሥት ዋና ዋና የኢኮኖሚ ምሰሶ ብለን የለየናቸው ሴክተሮችን ብንመለከት፤ ከፖሊሲ፣ከስትራቴጂ እና ከአፈጻጸም አንጻር ከፍተኛ ውጤት እያስገኙ ይገኛሉ ሲሉም አብራርተዋል። ለአብነትም ከኢንዱስትሪ አንጻር፤ ቀደም ሲል መንግሥት ኢንዱስትሪያል ፓርክ ይገነባ እንደነበር አውስተው አሁን ግን የኢንዱስትሪ ፓርክ መገንባት የሚችሉ የግል ሴክተሮች መፍጠር መቻሉን አንስተዋል። በርካታ ፋብሪካዎች፣ ኢንዱስትሪል ፓርኮች፣ ዘመናዊ ኢንዱስትሪዎች መሥራት ስንጀምርም፤ ከውጭ የምናስገባቸውን ምርቶች በሀገር ውስጥ በማምረት ወደ ውጭ የምንልከውን ቁጥርም ለማሳደግ በእጅጉ አግዘዋል ነው ያሉት።   ከግብርና አንጻር ኢትዮጵያ ውስጥ የነበረው ግብርና በርካታ ችግሮች እንደነበሩበት አውስተው፤ በሚሊዮን የሚቆጠር አርሶ አደርን በክላስተር በማደራጀት ትራክተር፣ ኮምባይነር፣ ፓምፕና የተለያዩ ማሽነሪዎችን ማቅረብ ስንችል አነስተኛ አርሶ አደሮች በሚያርሷቸው ማሳዎች ጭምር የሚገኘው ምርት አድጓል ብለዋል። የግል ሴክተሩም በዚያው ልክ ኢንቨስት ማድረግ እየጀመረ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። ለምሳሌ ቡናን ብንመለከት፤100 ሺህ ሔክታር ገደማ መሬት የግል ሴክተሩ ወስዷል፤ ይህን በመስኖ ከሠሩ የምናመርተውን ግማሽ ያህል ሊያመርቱ ይችላሉ ነው ያሉት። በአጠቃላይ በግብርናው ዘርፍ በርካታ ውጤቶች መገኘታቸውን በመግለጽ፤ይህም በፍጆታችን ብቻ ሳይሆን በኤክስፖርታችን የሚታይ ሆኗል ሲሉ አስገንዝበዋል። በማዕድን ዘርፍም፤ቀደም ሲል በዘርፉ ሊጠቀስ የሚችል ሥራ አለ ለማለት እንደሚከብድ በመጠቆም፤ ኤክስፖርቱም ውስን እንደነበር አንስተዋል። አሁን ግን በወርቅ፣ በማዳበሪያ፣ በጋዝ፣ በሴራሚክ፣ በሲሚንቶ ዘርፎች መንግሥት ዐይን ሲገልጥና ሲያመቻች የግል ሴክተሩ ተሳትፎ ምን ሊያመጣ እንደሚችል ውጤቱ ያሳያል ብለዋል። የማዕድን ሴክተሩ ፖሊሲ ላይ ባስቀመጥነው ልክ ውጤቱ በኤክስፖርት ውጤታችን ጭምር እየታየ ነው ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ከቴክኖሎጂ አንጻርም፤ እየተሠራ ያለው ሥራ ሞባይል ማስፋት፣ ዳታ ማስፋት ብቻ እንዳልሆነ አስገንዝበዋል። ስለሆነም በቴሌኮም ብቻ የነበረውን ሌላ ተቋም (ሳፋሪኮም) ስናመጣ ውድድር ሲጀመር፣ ኤ አይ ሲጨመር፣ መሶብ ሲታከል፣ 5 ሚሊየን ኮደሮች ሲጨመር ዘርፉ ኢኮኖሚያችንን የሚያነቃቃና የሚያስተሳስር እየሆነ መጥቷል ነው ያሉት በማብራሪያቸው። ከቱሪዝም አንጻርም ኢትዮጵያ ያላትን ታሪክና ባህል ማሳየት የሚያስችል መሠረተ-ልማት እንዳልነበረ አንስተዋል። ይህን እንቀይር የሚል እሳቤ ተይዞ ወደ ሥራ መገባቱንም በመግለጽ።   በዚህም መሠረት፤በገበታ ለሸገር፣በገበታ ለሀገር፣ በገበታ ለትውልድ ባለሃብት አስተባብረን የሠራናቸው ሥራዎች፤የቱሪዝም ሴክተሩን አስተምረን ዐይን ገልጠን ወደ ግል ሴክተር እንዲገባ ማድረግ አለብን የሚል ነበር ብለዋል። በዚህም በርካታ ቦታዎች በገበታ ኢንሼቲቭ መሠራታቸውን እና በዚያው ልክ የግል ሴክተሩ መግባቱን ጠቅሰዋል። በቅርቡ ለኮፕ 32 ስንወያይም አሁን 20 ሺህ ገደማ ያለው ለእንግዶች የሚሆን የአልጋ ዐቅማችንን ወደ 80 ሺህ ለማሳደግ የሚያስችሉ ሥራዎች ኢትዮጵያ ውስጥ እየተሠሩ መሆኑን አይተናል፤ይህም ትልቅ ስኬት ነው ብለዋል። በዚህ ላይ ኤርፖርቱ፣ኢነርጂው፣ መንገዱ እየተጨማመረ እየመገበው ሲሄድ፤ አጠቃላይ ፖሊሲውን በከፍተኛ ደረጃ አጉልቶ ያሳያል ነው ያሉት።
‎ሀዋሳ ከተማን የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከል በማድረግ ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግ ርብርብ እየተደረገ ነው 
Apr 19, 2026 190
‎ሀዋሳ ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡-ሀዋሳ ከተማን የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከል በማድረግ ከተማዋ አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ እንድትሆን ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የሲዳማ ክልል መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ ተናገሩ። የከተማዋ ሁለተኛ እና ሶስተኛ ዙር የኮሪደር ልማት ሥራ ማጠናቀቂያ የምስጋናና ዕውቅና እንዲሁም የአራተኛ ዙር የኮሪደር ልማትና የሐይቅ ዳርቻ ፕሮጀክት ማስጀመሪያ መርሀ ግብር ተካሄዷል፡፡   በመርሀ ግብሩ ላይም የሲዳማ ክልል መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሀም ማርሻሎ ‎ሀዋሳ ከተማን የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከል በማድረግ ከተማዋ አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ እንድትሆን ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። በከተማዋ ተጠናቀው ለአገልግሎት በበቁ የሁለተኛ እና ሶስተኛ ዙር የኮሪደር ልማት ሥራዎች የተሳተፉ አመራርና ባለሙያዎችን፣ የሥራ ተቋራጮችን እና በተለያየ መንገድ አስተዋፅኦ ያደረጉ የህብረተሰብ ክፍሎችን አመስግነዋል፡፡ ባለፉት የኮሪደር ልማት ሥራዎች እነዚህ አካላት፣ ልምዳቸውን፣ ዕውቀታቸውን፣ ገንዘባቸውንና ጉልበታቸውን በማስተባበር በቁጭት መስራታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ከተማዋ በሀገር እንዲሁም በአፍሪካ ደረጃ ተመራጭና ተወዳዳሪነቷ እንዲጨምር በቀጣይ ለሚከናወነው የኮሪደር እና የሐይቅ ዳርቻ ልማት ስራ ርብርባቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡   ዕውቅና ከተሰጣቸው የሥራ ተቋራጮች መካከል የይርጋዓለም ኮንስትራክሽን ባለቤት ወይዘሮ ይርጋዓለም አስፋው የተሰጣቸው ዕውቅና በቀጣይ ሥራዎች ላይ የላቀ ሥራ ለመስራት እንደሚያተጋቸው ተናግረዋል፡፡ በግል አስተዋፅዖ እውቅና ከተሰጣቸው የከተማዋ ነዋሪዎች መካከል ጋሻው ምትኬ (ዶ/ር) በበኩላቸው በተለይ በአረንጓዴ ልማት ሥራዎች ላይ የአፈር አይነት መረጣ፣ የሚተከሉ ዕፅዋት ልየታ እና እንክብካቤ እንዲሁም ከዚህ ጋር የተያያዙ ሌሎች ሙያዊ አበርክቶዎችን ያለክፍያ ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡ አሁን ላይ ከተማዋ አምራና ደምቃ ሲመለከቷት የህሊና እርካታ እንደሚሰማቸው ጠቅሰው ለከተማቸው በዚህ መልኩ ሙያዊ ተሳትፎ ማድረጋቸውን እንደ እድለኝነት እንደሚቆጥሩት ነው የተናገሩት፡፡ ‎አራተኛው ዙር የኮሪደር ልማት ስራ ከ3 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር በላይ እንደሚሸፍን የተገለጸ ሲሆን በከተማዋ በሚገኘው የፍቅር ሀይቅ ዙሪያ የሚከናወነው የሀይቅ ዳርቻ ልማት የዲዛይን ስራ በመጠናቀቁ በቅርቡ ወደ ግንባታ እንደሚገባም ተጠቁሟል።
ቱሪዝም የሀገራዊ ዕድገታችንን የወደፊት አቅጣጫ እየቀረጸ ያለ ዘርፍ መሆኑን እያስመሰከረ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) 
Apr 19, 2026 313
‎አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- ቱሪዝም የኢኮኖሚያችን አንዱ ምሰሶ እንደመሆኑ የሀገራዊ ዕድገታችንን የወደፊት አቅጣጫ እየቀረጸ ያለ ዘርፍ መሆኑን እያስመሰከረ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። የገበታ ለትውልድ መርሐ-ግብር አካል የሆነው በኦሮሚያ ክልል የሚገኘውን የሀሮ ደንዲ ሎጅ ዛሬ በይፋ መመረቃቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው አስታውቀዋል።   ‎ይህ ስፍራ የተፈጥሮን ሥነ-ምኅዳር የጠበቀ የቱሪዝም መዳረሻ ከመሆኑ ባለፈ፤ ዘመናዊ ሥነ-ሕንጻ ከተፈጥሮ የልብ ትርታ ጋር የተዋሃደበት የኢትዮጵያ አዲስ ገጽታ ነው ብለዋል። በዚህ ቦታ የቆመው ግንባታ ብቻ አይደለም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)፤ ይልቁንም የተፈጥሮ ቅርሳችንን በማክበር፣ የደንዲ ክሬተር ሐይቅን ነባራዊ ውበት ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተርፍ አድርገናል ሲሉ ገልጸዋል። ይህም የአካባቢውን ማኅበረሰብ ባህላዊ እሴት ባከበረ እና ሰው ተኮር በሆነ መልኩ መሬቱን ለመንከባከብና ማኅበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የተገነባ ስፍራ መሆኑንም ነው ያስገነዘቡት።   ‎የሀሮ ደንዲ ሎጅ፤ የገባነውን ቃል ፈጽመን የመገኘታችን ተጨማሪ ማረጋገጫ ነው ሲሉም አስረድተዋል። ሎጅው እና የአካባቢው አስደናቂ ሥነ-ምኅዳር ኢትዮጵያን ለመጎብኘት፣ ለኢንቨስትመንት እና ለሁነት ቱሪዝም ተመራጭ መዳረሻ ያደርጋታል በማለት ጠቅሰዋል። ‎ቱሪዝም የኢኮኖሚያችን አንዱ ምሰሶ እንደመሆኑ የሀገራዊ ዕድገታችንን የወደፊት አቅጣጫ እየቀረጸ ያለ ዘርፍ መሆኑን እያስመሰከረ ነው ሲሉም ተናግረዋል።
የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ የልማት ስኬቶች የሚያደርገውን ድጋፍ ይበልጥ እንደሚያሳድግ አስታወቀ
Apr 19, 2026 185
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፦የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ የተመዘገቡ የሪፎርም እና የልማት ስኬቶችን ለማስቀጠል የሚያደርገውን ድጋፍ ይበልጥ እንደሚያሳድግ አስታወቀ። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) እና የዓለም ባንክ ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብሰባ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ነው። በገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ ከስብሰባው ጎን ለጎን፣ከዓለም ባንክ የኦፕሬሽን ማኔጂንግ ዳይሬክተር አና ቤርዴ ጋር ውይይት አድርጓል።   ሚኒስትር አህመድ ሽዴ የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሪፎርም ሂደትና እያጋጠሙ ያሉ ዓለም አቀፋዊ ተጽዕኖዎችን በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን፤የልማት ስኬቶችን ዘላቂ ለማድረግ የዓለም ባንክ ድጋፉን እንዲያጠናክር ጠይቀዋል። ሚኒስትሩ የዓለም ባንክ የፋይናንስ አቅርቦቱን እንዲያሰፋና ፈጣን ምላሽ የሚሰጥ የድጋፍ ማዕቀፍ እንዲዘረጋ ጠይቀዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ መረጋጋትን ለማረጋገጥ በኢትዮጵያ መንግሥት፣በዓለም ባንክና በአይኤምኤፍ መካከል የተቀናጀ የድጋፍ ጥቅል ማሰባሰብ በሚቻልበት ሁኔታ ላይም ምክክር ተደርጓል። የዓለም ባንክ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አና ቤርዴ በበኩላቸው፣የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ ያለውን ጽኑ አጋርነት ያረጋገጡ ሲሆን፤ በዚህ ወሳኝ ወቅት ከልማት አጋሮች ጋር በመቀናጀት ተቋሙ ድጋፉን ይበልጥ ለማሳደግ ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ልዑክ በዕዳ ሽግሽግ ሂደቱ የተመዘገቡ ስኬቶችን አስመልክቶ ማብራሪያ የሰጠ ሲሆን፤ የዕዳ ዘላቂነትን ለማረጋገጥ ከግል አበዳሪዎች ጋር እየተደረገ ያለው ውይይት ውጤታማ መሆኑን ገልጿል። በተጨማሪም ሁለቱ ወገኖች በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን የኃይል ተጠቃሚ የሚያደርገውንና የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ሽግግር የማፋጠን አላማ ያለውን "Mission 300" የተሰኘ የኤሌክትሪክ ተደራሽነት መርሃ ግብር ተፈጻሚነት ለማጠናከር እንደሚሰሩ ገልጸዋል። ሁለቱ ወገኖች ለቀውሶች ፈጣን ምላሽ የሚሰጡ ድጋፎችን ለማቀላጠፍና ለኢትዮጵያ ሕዝብ ተጨባጭ የልማት ውጤቶችን ለማምጣት በጋራ ለመሥራት ጽኑ ቁርጠኝነት መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አስታውቋል።
በሸገር ከተማ የአገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታ እየተፈጠረ ነው
Apr 19, 2026 77
ሸገር፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በሸገር ከተማ ባለፉት ሦስት ዓመታት የአገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ለኢንቨስትመንት ሥራዎች ምቹ ሁኔታ መፍጠር መቻሉን የከተማዋ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ኃላፊ መኮንን አምባው ገለጹ። ኃላፊው ለኢዜአ እንዳሉት፤ መሶብ በሁሉም ዘርፎች በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚታዩ ማነቆዎችንና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመፍታት ለኢንቨስትመንት ሥራዎች መስፋፋት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል። ይህንን የአንድ ማዕከል አገልግሎት በይበልጥ ለማጠናከር የከተማው አስተዳደር በከተማ ደረጃ ብቻ ሳይሆን በክፍለ ከተሞችም ጭምር ተግባራዊ ለማድረግ እየሠራ መሆኑንም ጠቁመዋል። አገልግሎቱ ተገልጋዮች የሚፈልጉትን አገልግሎት በአንድ ቦታ በፍትሐዊነት እንዲያገኙ እያደረገ በመሆኑ የከተማዋን የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ይበልጥ ቀልጣፋ እያደረገው ነው ብለዋል። ይህንን ሥራ ይበልጥ ለማጠናከር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎቱን ወደ ተንቀሳቃሽነት በመለወጥ ዘርፉን በቅርበት ለማገልገል ሰፊ ሥራ መጀመሩንም አስታውቀዋል። በከተማዋ 32 የተለያዩ ሴክተሮችን በአንድ ማዕከል በማገናኘት ማኅበረሰቡ ቀልጣፋና ግልጽነት ያለው አገልግሎት በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲያገኝ እየተደረገ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በማዕከሉ 159 የሥራ ዓይነቶች አገልግሎት እየተሰጠባቸው መሆኑን ገልጸው፤ ከመደበኛ የሥራ ቀናት በተጨማሪ በምሳ ሠዓትና በእሁድ ቀናትም አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን አረጋግጠዋል። በሸገር ከተማ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ለተገልጋዮች ምቹ ሁኔታን የፈጠረና የአገልግሎት አሰጣጥ ዕርካታን ያረጋገጠ መሆኑን የከተማዋ ተገልጋዮች ገልጸዋል።
ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ለኢትዮጵያ የሪፎርም አጀንዳዎች ቀጣይነት ያለውን ጠንካራ ድጋፍ አረጋገጠ
Apr 19, 2026 80
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይ ኤም ኤፍ) ኢትዮጵያ ያከናወነችው ሪፎርም ያመጣውን መሻሻል በማድነቅ ለሀገሪቱ የሪፎርም አጀንዳ ያለውን ጠንካራ ድጋፍ ዳግም አረጋግጧል። በገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ዋና ዳይሬክተር ክሪስታሊና ጆርጂየቫ ጋር ተወያይቷል። ውይይቱ የተካሄደው፤ ከ2026 የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም የፀደይ ስብሰባ ጎን ለጎን መሆኑን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ የላከው መረጃ አመላክቷል። በምክክሩ ወቅትም፤ በኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ አማካኝነት እየተመዘገቡ ያሉ ቀጣይነት ያላቸው ውጤቶችን ልዑኩ አብራርቷል። ለአብነትም በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ጠንካራ የኢኮኖሚ ዕድገትና የዋጋ ግሽበት መቀነስን ጨምሮ ሌሎች አዎንታዊ አዝማሚያዎች መታየታቸውን ጠቁሟል። ሪፎርሙ በመካከለኛው ምሥራቅ የተከሰተውን ወቅታዊ ሁኔታ ጨምሮ የሚከሰቱ ውጫዊ ተፅዕኖዎችን ተቋቁሞ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉም ተብራርቷል። ወቅታዊ ዓለም አቀፋዊ ችግሮች ከአቅርቦት ሰንሰለት መስተጓጎል፣ ከነዳጅ ብሎም ማዳበሪያ ዋጋ መናር ጋር ተያይዞ ጫናዎች መኖራቸውም እንዲሁ። እነዚህን ወቅታዊ ችግሮች ለመሻገርም የተጠናከረ ዓለም አቀፍ ድጋፍ አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝቧል። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ዋና ዳይሬክተር ክሪስታሊና ጆርጂዬቫ በበኩላቸው፥ ኢትዮጵያ ያከናወነችው ሪፎርም ያመጣውን መሻሻል በማድነቅ፤ተቋማቸው ከዓለም ባንክ ጋር በመተባበር ሪፎርሙን ለማስቀጠል እና የፋይናንስ ፍላጎቶችን ለማሟላት ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጠዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የሐዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የማኅበራዊ ትሥሥር መሰረት እየሆነ ነው 
Apr 19, 2026 64
ሐዋሳ፤ ሚያዝያ 11/2018 (ኢዜአ)፡- የሐዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የተፈጥሮ ፀጋዋን ከማጉላቱ ባለፈ የማኅበራዊ ትሥሥር መሰረት መሆኑን የከተማዋ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለፁ። የሐዋሳ ከተማ 2ኛና 3ኛ ዙር የኮሪደር ልማት ሥራ ማጠናቀቂያ እና የ4ኛ ዙር የኮሪደርና የሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ማስጀመሪያ መርሐ-ግብር ተካሂዷል። ‎በዚሁ ወቅት ከንቲባው እንዳሉት፤ የሐዋሳን የቱሪዝምና ኮንፈረንስ ማዕከልነት ለማጠናከር ሥራዎች በተሻለ ፍጥነትና ጥራት መከናወናቸው ይቀጥላል። ‎የከተማዋ የኮሪደር ልማት ያላትን የተፈጥሮ ፀጋ አጉልቶ ከማውጣቱ በተጨማሪ፤ የቱሪዝም መስኅብና የማኅበራዊ ትሥሥር መሠረት እየሆነ ነው ብለዋል። ‎ የግንባታ ሥራው ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቃው የኮሪደር ልማት ሥራ የከተማዋን ውበትና የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጠ መሆኑንም አንስተዋል። 4ኛው ዙር የኮሪደር ልማት 3 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር እንደሚሸፍን ጠቁመው፤ የሐይቅ ዳርቻ ልማቱም የሐዋሳ ሐይቅ ዳርቻን ይዞ እንደሚለማ አመላክተዋል።
የኢትዮጵያ የመሰረተ ልማት ስኬት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፉን የሚያሳልጥ ወሳኝ ዕድል ፈጥሯል
Apr 18, 2026 358
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የመሰረተ ልማት ስኬት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፉን የሚያሳልጥ ወሳኝ ዕድል መፍጠሩን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክ ሚኒስትር ዴኤታ ዴንጌ ቦሩ ገለጹ። ''ኢትዮጵያ ትገነባለች፤ ፈጠራ፣ ፍጥነትና ጥራት ለመሰረተ ልማት እመርታ'' በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ የመሰረተ ልማትና ኮንስትራክሽን ሳምንት እየተካሄደ ይገኛል።   በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ሁለተኛ ቀኑን ይዞ በቀጠለው መድረክ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መሰረተ ልማት ትስስርና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ውይይት ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ዴንጌ ቦሩ፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያሳልጡ የመሰረተ ልማት ስኬቶች ተመዝግበዋል ብለዋል። እነዚህ ስኬቶችም የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ውጤታማነትን በማሻሻል አዲስ የኢኮኖሚ ዕድገት የለውጥ ምዕራፍ መክፈቱን ገልጸዋል። በቀጣይም የተቋማትን ቅንጅት በማጠናከር የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ትስስርን የሚያሳልጡ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።   የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መሀመድ አብዱራህማን የኢትዮጵያ መንገዶች ግንባታ እስከ ኤክስፕረስ መንገድ ያለው ዕምቅ አቅምና ቀጣይ ተስፋ የሚል የመነሻ ጽሁፍ አቅርበዋል። በጽሑፋቸውም፤ የኢትዮጵያ መንገዶች እ.አ.አ. በ1997 ከነበረበት 26 ሺህ 550 ኪሎ ሜትር በ2025 ከ180 ሺህ ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ጥራት ያለው የመንገድ መሰረተ ልማት መገንባቱን አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ የመንገድ ልማት ሽፋንም ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን በማፋጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም የመንግስት፣ የልማት አጋሮችንና ዓለም አቀፍ ተቋማትን የበጀት ትብብር በማጠናከር እ.አ.አ በ2030 የመንገድ ሽፋንን 245 ሺህ ኪሎ ሜትር ለማድረስ እየተሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል።   የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ኢንጂነር ህሊና በላቸው፤ የኢትዮጵያን የባቡር ልማትና ቀጣናዊ ትስስር የሚዳስስ የመወያያ ጽሁፍ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ የኤሌክትሪክ ኃይል የባቡር መሠረተ ልማት የኢኮኖሚ ዕድትን በማፋጠን ቀጣናዊ ኢኮኖሚ ትስስርን ለማጠናከር የማይተካ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። በቀጣይም የባቡር መሰረተ ልማት ሥራዎችን የሚያፋጥን ብቁ የሰው ሃይል ለማፍራት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።   በመድረኩ በገጠር ትስስር ዙሪያ የመወያያ ጽሁፍ ያቀረቡት መሀመድ አሚን በበኩላቸው፤ የከተማና ገጠር ማህበራዊና ኢኮኖሚያ ትስስርን የሚያጠናክር የመንገድ መሰረተ ልማት እየተገነባ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የመንገድ መሰረተ ልማት ትስስር የአርሶና አርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያሳለጠ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 95 ሺህ ወጣቶች በተለያዩ የስራ መስኮች ተሰማርተዋል
Apr 18, 2026 90
ነቀምቴ ፤ሚያዚያ 10/2018 (ኢዜአ)፡-በምስራቅ ወለጋ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት 95 ሺህ ወጣቶች ተደራጅተው በተለያዩ የስራ መስኮች መሰማራታቸውን የዞኑ የስራ እድል ፈጠራ እና ክህሎት ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ባጩ ተስፋዬ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ጽሕፈት ቤቱ የሥራ አጥነትን ችግር በማቃለል የአምራች ኃይሉን የልማት ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየሠራ ይገኛል። በበጀት ዓመቱም ከ100 ሺህ የሚበልጡ ወጣቶችን በማደራጀት ወደ ሥራ ለማስገባት የታቀደ ሲሆን፣ እስካሁን ባለው ሒደት 95 ሺህ ወጣቶችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። ወጣቶቹ ከተሰማሩባቸው መስኮች መካከል ግብርና እና ማኑፋክቸሪንግን ጨምሮ ሌሎች የገቢ ማስገኛ ፕሮግራሞችን በአብነት ጠቅሰዋል። ወጣቶቹ በተሰማሩባቸው መስኮች ውጤታማ መሆን እንዲችሉም መንግሥት ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር እንዳመቻቸላቸው ተናግረዋል። ይህም የዞኑን ወጣቶች የሥራ ባሕል በመቀየር የልማት ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ መደላድል መፍጠሩን ገልጸዋል። በዞኑ የሲቡ ስሬ ወረዳ የንግድ፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ኢንቨስትመንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኢብሳ ዲለንሳ በበኩላቸው፤ ወጣቶች ከጠባቂነት ተላቀው ባላቸው ዕውቀት እና ጉልበት ሠርተው እንዲለወጡ በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህ ረገድ በበጀት ዓመቱ ከ9 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለማመቻቸት ታቅዶ ሲሠራ መቆየቱን ጠቅሰዋል። ወጣቶቹን በ340 ኢንተርፕራይዞች በማደራጀት በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በእንስሳት ማደለብና እርባታ፣ እንዲሁም በሌሎች መስኮች በመሰማራት የተሻለ ውጤት በማምጣት ላይ እንደሚገኙ አስረድተዋል። የወረዳው አስተዳደርም ከ37 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር በማቅረብ ኢንተርፕራይዞቹ እንዲጠናከሩ ድጋፍ ማድረጉን አብራርተዋል። ከሥራ ዕድሉ ተጠቃሚዎች መካከል በብረታ ብረትና እንጨት ሥራ የተሰማራው ጪምዴሳ በዳሳ እንደሚለው፤ በዚህ ዓመት መንግሥት ባመቻቸላቸው ዕድል የ200 ሺህ ብር ብድር በመውሰድ ሥራ ጀምረዋል። በተመቻቸላቸው ዕድል ጠንክረው በመሥራትም ከራሳቸው አልፎ ለሌሎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ይናገራል። በአሁኑ ወቅትም ካፒታላቸውን ወደ 1 ሚሊዮን ብር በማሳደግ ተጠቃሚ መሆናቸውን አመልክቷል። በወረዳው የሚገኙት የጫልቱ፣ ዓለምነሽ እና ጓደኞቻቸው ማህበር አባል ወጣት ምቲኬ አበራ፤ በተያዘው ዓመት በእንጀራ ንግድ ላይ ሥራ የጀመረው ማኅበራቸው ጥሩ ገቢ ማግኘት መጀመሩን ተናግራለች።  
በአምቦ ከተማ ከ900 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች ወደ ሥራ ገብተዋል
Apr 18, 2026 127
አምቦ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በአምቦ ከተማ በዘጠኝ ወራት ከ900 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ወደ ስራ መግባታቸውን የከተማ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በአምቦ ከተማና አካባቢው በተለይም የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴውን በተመለከተ የከተማ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጂፋራ ጫልችሳ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። ከለውጡ በኋላ በዘርፉ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በርካታ ባለሃብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች በመሳተፍ ለብዙ ወገኖች የስራ እድል እየፈጠሩ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በማኑፋክቸሪንግ፣ በአግሮ እንዱስትሪ፣ በአገልገሎት እና ሌሎችም መስኮች በብዛት እየተሳተፉ መሆኑን አንስተው፤ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራትም ከ900 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች ወደ ስራ ገብተዋል ብለዋል። ከከተማዋ መዘጋጃ ቤት ጋር በመተባበር የመሰረተ ልማትና የመሬት አቅርቦት እንዲሁም ምቹ አገልግሎት እንዲኖር መሰራቱን አስታውሰው በዚህም አልሚዎች እየተበራከቱ መጥተዋል ብለዋል። በዘንድሮው በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት ብቻ 42 ሄክታር መሬት ለአልሚዎች መሰጠቱን ለአብነት ጠቅሰዋል።
በዞኑ ሞዴል አርሶ አደሮችን ወደ ኢንቨስትመንት የማሻገር ስራ እየተሰራ ነዉ
Apr 18, 2026 125
ጅማ፤ ሚያዚያ 10/2018(ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን ሞዴል አርሶ አደሮችን እና በጥቃቅንና አነስተኛ ተደራጅተዉ ስኬታማ የሆኑ ማህበራትን ወደ ኢንቨስትመንት የማሸጋገር ስራ እየተካሔደ ነዉ። በጅማ ዞን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሰፋፋ የመጣዉን የመሠረተ ልማት ግንባታ ተከትሎ በኢንቨስትመንት የሚሰማሩ ባለሀብቶች ቁጥር እየጨመረ መሆኑም ተገልጿል። በተያዘው ዓመትም 1 ሺህ 680 ፕሮጀክቶችን ወደ ስራ ማስገባቱን የዞኑ ኢንቨስትመንት እና ኢንዱስትሪ ፅህፈት ቤት አመልክቷል። የፅህፈት ቤቱ ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ዘሊካ ቡላ ለኢዜአ እንደተናገሩት ፤በተያዘው ዓመት በጥቃቅንና አነስተኛ የተደራጁ 20 ማህበራት፣ 39 የህብረት ስራ ማህበራትን ጨምሮ በድምሩ 1 ሺህ 680 ፕሮጀክቶች ወደ ኢንቨስትመንት ገብተዋል። ወደ ኢንቨስትመንት ከገቡት 1 ሺህ 680 ፕሮጀክቶች ውስጥ ደግሞ 1 ሺህ 621 የሚሆኑት ሞዴል አርሶ አደሮች መሆናቸውን ነው የገለጹት፤ ወደ ኢንቨስትመንት የገቡት ባለሃብቶችም 4 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ መሆናቸዉንም ነው ያመለከቱት። ለኢንቨስትመንት ስራዉ 7 ሺህ 578 ሄክታር መሬት መሰጠቱን የገለፁት ስራ አስኪያጇ ለፕሮጀክቶቹ ተግባራዊነት ጠንካራ የሆነ ክትትልና ደጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑንም ጠቅሰዋል። በዞኑ ለኢንቨስትመንት መሬት ተረክበዉ ወደ ስራ መግባት ያልቻሉትን በመለየትም የፋይናንስ እና የሊዝ ማሽን አቅርቦት ችግር ያለባቸውን በመለየት ከባንክ ብድር የሚያገኙበትን ሁኔታ ለማመቻቸት እየተሰራ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ሙያዊ ክትትልና ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑን አመልክተው አስፈላጊዉ ድጋፍ ተደርጎላቸዉ ወደ ስራ መግባት ያልቻሉ ባለሀብቶች ፍቃዳቸዉ የሚሰረዝበት አሰራር ተግባራዊ እንደሚደረግም ነው የጠቀሱት። በሌላ በኩል በተቋም ደረጃ አገልግሎት አሰጣጥን የማዘመን እና የማቀላጠፍ ስራ ትኩረት የተሰጠዉ ሲሆን ፣ ከዚህ ቀደም የነበሩ የተንዛዙ አሰራሮችን በማስቀረት የተሻለ አገልግሎት እየተሰጠ ነዉ ብለዋል።  
በክልሉ ከ919 ሺህ የሚበልጡ ዜጎች በተለያዩ መስኮች የስራ እድል አገኝተዋል
Apr 18, 2026 100
ባህር ዳር፤ ሚያዚያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ከ919 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች በተለያዩ መስኮች የስራ እድል መፈጠሩን የክልሉ ስራና ስልጠና ቢሮ ገለጸ። ‎የቢሮው የስራ ዕድል ፈጠራና ኢንተር ፕራይዞች ልማት ዳይሬክተር አቶ ስላባት ሰውአገኝ ለኢዜአ እንደገለፁት ዜጎችን የስራ እድል ተጠቃሚ ለማድረግ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው። በዚህም በበጀት ዓመቱ አንድ ነጥብ አንድ ሚሊዮን ለሚጠጉ ዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር ግብ ተይዞ በተደረገ ሁሉን አቀፍ ጥረት በዘጠኝ ወሩ ለ919 ሺህ 475 ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልፀዋል። የስራ ዕድሉ ከተፈጠረባቸው መስኮች መካከልም ከ125 ሺህ 300 በላይ የሚሆኑት በውጭ ሀገር የስራ ስምሪት መሆኑን ገልጸዋል። የስራ ዕድሉ በግብርና፣ በኢንዱስትሪና በአገልግሎት ዘርፎች መሆኑን ገልጸው፤ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት በድምሩ ለ919 ሺህ 475 ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል። ዳይሬክተሩ እንዳሉት 1 ሺህ 347 የመስሪያ ሼዶች እንዲሁም ለከተማ ግብርና፣ ለማዕድን ማውጫና ለሌሎች የግብርና ልማት ተግባራት 11 ሺህ 444 ሄክታር መሬት ለኢንተርፕራይዞች መተላለፉንም ተናግረዋል። ‎የመስሪያ ገንዘብ ለሚያስፈልጋቸው ኢንተርፕራይዞች ከ5 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ የብድር አቅርቦት የተመቻቸ ስለመሆኑም አንስተዋል።
በአማራ ክልል የበልግ ወቅት እስካሁን ከ241 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ ሰብሎች እየለማ ነው
Apr 18, 2026 91
ደሴ ፤ሚያዚያ 10/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የበልግ ወቅት እስካሁን ከ241 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ ሰብሎች መልማቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ ግብርና ቢሮ የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማንደፍሮ አስላከ (ዶ/ር)፤ በክልሉ ምርታማነትን ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትንና የዘንድሮውን የበልግ ወቅት ልማት በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በማብራሪያቸውም የክልሉን የግብርና ዘርፍ በማዘመን ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥና ከተረጅነት የመውጣት ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። በያዘነው የበልግ ወቅት ከ245 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት መታቀዱን አስታውሰው እስካሁን ከ241 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ ሰብሎች መሸፈን ተችሏል ብለዋል። አሁን እየጣለ ያለው የበልግ ዝናብ ለሰብል ልማት ተስማሚ በመሆኑ በተለይም የስንዴ፣ ገብስ፣ ጤፍ፣ ቦለቄ፣ ማሾ፣ አተር፣ ምስርና ሌሎችንም ሰብሎች መዝራት ስለመቻሉ ተናግረዋል። የልማት ጥረቱ ተጠናክሮ መቀጠሉን የገለጹት ዶ/ር ማንደፍሮ በበልጉ የተያዘውን እቅድ ለማሳካት የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የሰሜን ሽዋ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ ችሮታው አስፋው፤ በዞኑ ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የአካባቢውን ምቹነት መሰረት ያደረጉ የግብርና ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የበልጉን ዝናብ በመጠቀም በዞኑ እስካሁን ከ86 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን ጠቅሰው ከዚህም ከ1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት የሚገኝ ይሆናል ብለዋል። በደቡብ ወሎ ዞን የተሁለደሬ ወረዳ እና በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ደዋጨፋ ወረዳ የኢዜአ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አርሶ አደሮች በዘንድሮው የበልግ ውቅት የእስካሁኑ እንቅስቃሴ ጥሩ መሆኑን አንስተው ከፍተኛ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በመጪው ክረምት ሚተከሉ ከ916 ሺህ በላይ የቡና ችግኞች ተዘጋጅተዋል
Apr 18, 2026 109
ደብረ ማርቆስ ሚያዚያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን በመጪው ክረምት ሚተከሉ ከ916 ሺህ በላይ የቡና ችግኞች መዘጋጀታቸው ተገለፀ። በዞኑ ግብርና መምሪያ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ባለሙያ አቶ ተሾመ በላይ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤ በመጪው የክረም ወር ከ320 ሄክታ በላይ በሆነ መሬት ላይ የሚተከሉ 916 ሺህ የቡና ችግኞች ተዘጋጅተዋል። በዋናነትም የአካባቢውን ስነ ምህዳርና የአየር ንብረት ተስማሚነት በማረጋገጥ ለቡና ልማት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ገልፀዋል። በቡና ልማቱም ከ25 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ ከ320 ሄክታር በላይ መሬትን ለመሸፈን ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። ችግኞቹ በመንግስት፣ በማህበራትና በግለሰቦች የችግኝ ጣቢያዎች ፈልተው የተዘጋጁ መሆኑንም ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩን በተለያዩ የግብርና አማራጮች በማሳተፍ የምግብ ዋስትናውን ለማረጋገጥ እንዲችል ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ገልፀዋል። በዞኑ በደብረ ኤሊያስ፣ በማቻከልና በጎዛምን ወረዳዎች በኩታ-ገጠም እየተካሄደ ያለውን የቡና ልማት በማጠናከር በቀጣይ በሁሉም ወረዳዎች ተደራሽ የማድረግ ተግባራት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በማቻከል ወረዳ የውላ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አብነት ይርዳው፤ ቡናን በኩታ ገጠም ለማልማት ከግማሽ ሄክታር በላይ መሬት እያዘጋጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ገነት አያሌው በበኩላቸው ከዚህ ቀደም ካለሙት ቡና እያገኙ ያለውን ጥቅም ለማስፋት በክረምቱ የሚተከል ከሩብ ሄክታር በላይ ማሳቸውን እያዘጋጁ መሆናቸን ገልጸዋል። ለዚህም ከ6 ሺህ በላይ የቡና ችግኞችን ማፍላታቸውን ጠቁመው ከራሳቸው የሚተርፈውን በመሸጥ ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት አቅደው እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት በተደረገ ጥረት ከ5 ሺህ 300 ሄክታር በላይ መሬት በቡና መልማቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ሕይወትን መለወጥ እንደሚቻል በተግባር እያረጋገጠ ያለው የከተማ ግብርና
Apr 17, 2026 390
የሌማት ትሩፋት አካል በሆነው የከተማ ግብርና በመሰማራት ሕይወትን መለወጥ እንደሚቻል በተግባር እያሳየን ነው ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው በዘርፉ የተሰማሩ የመዲናዋ ነዋሪዎች ገለፁ። የከተማ ግብርና በከተማ ውስጥ በሚገኙ አነስተኛ ቦታዎች፣ መኖሪያ ግቢዎች፣ ጣራዎች ወይም አጥሮች ላይ ቀላል ቁሳቁሶችንና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም አትክልት፣ ፍራፍሬ፣ እንስሳትና ዓሳ በማምረት ህይወታቸውን የሚቀይሩበት የምርት ስርዓት ነው። ይህ ዘርፍ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የኑሮ ውድነትን ከመቀነስ ባለፈ ለሴቶችና ለወጣቶች ሰፊ የስራ ዕድልን በሰፊው የሚፈጥር ነው፤ በመፍጠር ላይም ይገኛል። መንግሥት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ወደ ተግባር የገባው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርም በገጠርም ሆነ በከተማ ዜጎች የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ በማድረግ ረገድ አመርቂ ውጤቶችን በማስመዝገብ ላይ ነው። በአዲስ አበባ በከተማ ግብርና የተሰማሩ ተጠቃሚዎችም በዘርፉ መሰማራታቸው የዕለት ተዕለት የቤት ፍጆታቸውን ከመሸፈን አልፎ አዋጭ የገቢ ምንጭ በመሆን ሕይወታቸውን በተጨባጭ እየቀየረላቸው እንደሚገኝ ነው ለኢዜአ የሚገልጹት።   በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ላይ የተሰማራው የወልዳ ወሊኒ ማህበር ሰብሳቢ ተካልኝ ደበሌ በ2014 ዓ.ም መንግሥት ለከተማ ግብርና ስራ የሰጠውን ትኩረት ተከትሎ ማህበራቸው ወደ ከተማ ግብርና ስራ መግባቱን ይገልጻሉ። ማህበሩ በአሁኑ ሰዓት ሰባት አባላት ያሉት መሆኑን በመጠቆም የተለያዩ የአትክልት ምርቶችን በማምረት ለራስ ፍጆታ ከማዋል ባለፈ ለማህበረሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የከተማ ግብርና ስራ በስፋት ያላተለመደ ተግባር እንደነበረ አንስተው፤ አሁን ላይ በግብርና ስራ ላይ የሚሰማሩ ነዋሪዎች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን ያነሳሉ።   ሌላኛው በእንስሳት እርባታ ላይ የተሰማራው ወጣት አወቀ አበባው እንደሚለው ዶሮዎችንና የወተት ላሞችን በማርባት ተጠቃሚ በመሆን ላይ ነው። እንቁላል እና የተለያዩ ወተትና የወተት ተዋጽኦ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማህበረሰቡ በማቅረብ ገበያ የማረጋጋት ስራ እየሰሩ መሆኑን ይናገራል። በዘርፉ የተሰማሩት እነዚህ ተጠቃሚዎች፣ በከተማ ግብርና ተሰማርቶ ውጤታማ መሆን እንደሚቻል በተጨባጭ እያረጋገጡ መሆኑን ያስረዳሉ። ሌሎች ዜጎችም መልካም ተሞክሮዎችን በመቀመርና በአካባቢያቸው ያለውን ሀብት በመጠቀም፣ የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የገቢ ምንጫቸውን እንዲያሳድጉ ጥሪ አቅርበዋል።   በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የእንስሳትና ሀብትና መኖ ልማት ባለሙያ አሰፉ ሙላቱ እና የሆርቲካልቸር ባለሙያው ማሙሽ አሳምነው እንደሚሉት በመዲናዋ የከተማ ግብርና ስራ ባህል እየሆነ መምጣቱን ይገልጻሉ።   በዘርፉ የተሰማሩ አካላት የተሻሻሉ ምርት ዝርያዎችን መጠቀም እንዲችሉ፣ምርትን ሲያመርቱ ደህንነቱን በጠበቀ መልኩ እንዲሆን ሙያዊ እገዛዎችን እያደረጉ እንደሚገኙ ገልጸው፤ ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።    
በኢትዮጵያ የተስማሚነት ምዘና ድርጅት የሚሰጡ አገልግሎቶችን ዓለም አቀፍ ቅቡልነት የሚያረጋግጥ አቅም እየተፈጠረ ነው
Apr 17, 2026 346
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ የተስማሚነት ምዘና ድርጅት የሚሰጡ የፍተሻ፣ የኢንስፔክሽንና የሰርተፊኬሽን አገልግሎቶችን ዓለም አቀፍ ተቀባይነት የሚያረጋግጥ አቅም እየተገነባ መሆኑን የድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መዓዛ አበራ ገለጹ። ኢንጂነር መዓዛ አበራ እንደገለጹት፤ ተቋሙ የሀገሪቱን ምርቶችና አገልግሎቶች የጥራት ደረጃ በማረጋገጥ በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማስቻል እየሰራ ነው። በአሁኑ ወቅትም 124 የላብራቶሪ ፍተሻ ወሰኖች በዕውቅና ሰጭ አካል ኦዲት ተደርጎ ውጤቱ እየተጠበቀ መሆኑን ገልጸዋል። በኢንፔክሽን ዘርፍ በተሰራ ስራም በግብርና ምርት፣ በታሸጉ ምግቦች፣ በኬሚካል፣ በዌር ሀውስና በሊፍት ኢንስፔክሽን 16 ወሰኖችን ማስጠበቅ እንደተቻለ ተናግረዋል። በዘንድሮው ዓመትም በታወር ክሬን፣ በቧንቧ ውሃ ናሙና እንዲሁም በዘይትና በዱቄት ቫይታሚን ማበልጸግ ዘርፎች ተጨማሪ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ለማግኘት ማመልከቻ መቅረቡን ጠቁመዋል። በሰርተፊኬሽን ዘርፍም 47 ነባር የዓለም አቀፍ ዕውቅናዎችን በማስጠበቅ በዘንድሮው ዓመት ብቻ በ16 አዳዲስ ወሰኖች ላይ ዕውቅና ማግኘት መቻሉን አስታውቀዋል። በተጨማሪም 23 ወሰኖችን በመለየት ለዓለም አቀፍ ዕውቅና የሚረዳ የሰነድ ዝግጅትና የአቅም ግንባታ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ አንስተዋል። በዘንድሮ ዓመትም በአሉሚኒየም፣ በቆርቆሮ፣ በሚስማርና በሴራሚክ ምርቶች ላይ አዲስ ዕውቅና መገኘቱን ተናግረዋል። በአካባቢ ጥበቃና በትምህርት አስተዳደር ሥርዓት የተገኘው ዓለም አቀፍ ዕውቅናም ድርጅቱ የሚሰጣቸውን አገልግሎት በማንኛውም ዓለም ተቀባይነት እንዲኖረው የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰዋል። በመጨረሻም ድርጅቱ ግቦችን ለማሳካት ከብሔራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት እንዲሁም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝ አብራርተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም