ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የመገጭ ግድብ የመደመር መንግስት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅም ማሳያ ነው
Aug 25, 2026 189
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦የመገጭ ግድብ የመደመር መንግስት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅም ማሳያ መሆኑን የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ገለጹ። የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የመገጭ ግድብ ግንባታ ያለበትን ደረጃ ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ተቋማት ለተውጣጡ ጋዜጠኞች አስጎብኝቷል። የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ጉብኝቱን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፤የመገጭ ግድብ የጎንደር ከተማ የዘመናት ጥያቄ መሆኑን ገልጸዋል። የመገጭ ግድብ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ለሕዝቡ ያልተሠራውን ተሠራ እየተባለ 18 ዓመታትን ማስቆጠሩን ጠቅሰዋል። መገጭ ለንጹህ መጠጥ ውሃና ለመስኖ ልማት በመዋል ለኢትዮጵያ ብዙ ጥቅም ማስገኘት የሚችል ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። ነገር ግን ፕሮጀክቱ በአግባቡ ባለመመራቱ፣ በጋ ላይ የተሠራው ክረምት ላይ በጎርፍ እየተናደ ለአካባቢው ማኅበረሰብ የሕልውና ሥጋት፣ ለጣና ሐይቅ ደግሞ በደለል መሞላት ምክንያት ሆኖ ቆይቷል ብለዋል። ይሁን እንጂ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር ሰጭነት ፕሮጀክቱን እንደገና በማጥናት ሕዝብ ከባዶ ተስፋ ወደሚጨበጥ ሕልም ማምጣት እንደተቻለ ገልጸዋል። ይህም ለሕዝቡ ከሚሰጠው ቀጥተኛ ጥቅም ባለፈ፣ ዓባይ ወንዝና ጣና ሐይቅን ከደለል በመታደግ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት እንዳለው በተግባር ገልጧል ብለዋል። በመገጭ ግድብ ግንባታ የታየው ፈጣን የግንባታ ለውጥ የመደመር መንግሥት ፕሮጀክት ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅሙን በተግባር ያሳየበት መሆኑን ገልጸዋል። የመገጭ ግድብ ሰፊ የእርሻ መሬት ላለው የደንቢያ አካባቢ የልማት ተስፋ፤ ለጎንደር ከተማ ደግሞ የዘላቂ ንጹህ መጠጥ ውሃ ብስራት ይሆናል ብለዋል። ሕብረተሰቡ የግድቡን አስፈላጊነት በወጉ በመረዳት አካባቢውን በንቃት እየጠበቀ፣ የፕሮጀክቱን አፈጻጸም በቅርበት እየተከታተለው መሆኑን ገልጸዋል። ለ18 ዓመታት ሕዝቡን በባዶ ተስፋና በጎርፍ ሲያማርር የነበረው የመገጭ ግድብ፣ ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግንባታው ተጠናቆ በቅርቡ ይጠናቀቃል ብለዋል።  
የአፍሪካን የጤና ሥርዓት በራስ አቅም ለማዘመን የአባል ሀገራትን ትብብር ማጠናከር አስፈላጊ ነው
Aug 25, 2026 204
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካን የጤና ሥርዓት በራስ አቅም ለማዘመን ኢንቨስትመንትንና የአባል ሀገራትን ትብብር ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር መሐመድ ያኩብ ጃናቢ ገለጹ። 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባኤ በአዲስ አበባ ዓድዋ ድል መታሰቢያ እየተካሄደ ይገኛል። የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር መሀመድ ያኩብ ጃናቢ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ 76ኛ የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባኤ በአንድ መድረክ ከመወያየት በላይ ነው። መድረኩ የአፍሪካ የጤና ችግሮች ላይ የጋራ ውይይት በማድረግ የጋራ የመፍትሔ ሀሳብ የሚፈልቅበት መሆኑን ገልጸዋል። በአፍሪካ በመሪዎች ቁርጠኝነት፣ በጤና ተቋማትና ባለሙያዎች ዝግጅት እንዲሁም በማህበረሰቡ ትብብር በጤና ስርዓቱ ላይ መሻሻል ታይቷል ብለዋል። አፍሪካ ከ1 ነጥብ 5 ቢሊየን በላይ ህዝብ ምድር መሆኗን በማንሳትም፤ አፍሪካ የጤና ስርዓቷን በራሷ አቅም ለመገንባት ጠንካራና ቀጣይነት ያለው የጤና ተቋማትን መገንባት ይገባታል ነው ያሉት። በአፍሪካ ለተመዘገበው የጤና አገልግሎት መሻሻል የዓለም ጤና ድርጅት ያልተቋረጠ ድጋፍ ማድረጉን በመግለፅ፤ የአፍሪካ የጤና ኢንቨስትመንትን በራስ አቅም መፍጠር አስፈላጊ ነው። የአፍሪካ ራዕይ ግልጽ ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የጤና ልህቀት ማዕከል መገንባትና የጤና ስርዓቷን በራሷ አቅም መገንባት መሆኑን በመግለጽ። አህጉሪቱ የዕወቀትና የተፈጥሮ ሀብት ችግር የለባትም፤ መሰረታዊው ጉዳይ ተደራሽነትን ማስፋት የሚያስችል የጤና አገልግሎት መስጠት ነው ሲሉም ገልጸዋል። የጤና ሥርዓት ዝማኔ አመራር፣ ኢንቨስትመንትና ትብብር እንደሚጠይቅ ጠቁመውም፤ የዓለም ጤና ድርጅት አፍሪካ አቅሟን እንድትገነባ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።  
የመገጭ ግድብ ግንባታ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ ደርሷል
Aug 25, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ጎንደር ከተማ አቅራቢያ እየተገነባ የሚገኘው የመገጭ ግድብ ፕሮጀክት ግንባታ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ መድረሱን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ የመገጭ የግድብ ግንባታ ያለበትን ደረጃ ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ለተውጣጡ ጋዜጠኞች አስጎብኝቷል። ሚኒስቴሩ የኢትዮጵያን በምግብ ራስን የመቻል ጉዞ የሚያሳኩ የመስኖ ልማት መሰረተ ልማቶችን እያስፋፋ ይገኛል። ከእነዚህ መሰረተ ልማቶች መካከል በአማራ ክልል ጎንደር አቅራቢያ እየተገነባ የሚገኘው መገጭ ግድብ አንዱ ሲሆን ግድቡ ከተጀመረ ረዘም ያለ ጊዜ አስቆጥሯል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ግድቡ በፍጥነት ተጠናቆ አገልግሎት እንዲሰጥ ባስቀመጡት አቅጣጫ መሰረትም በተለይ ባለፉት ሁለት ዓመታት ግድቡን ለማጠናቀቅ በተደረገው ርብርብ አሁን ላይ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ ደርሷል። በመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የመስኖ ፕሮጀክቶች ፕሮግራም ጽህፈት ቤት ስራ አስኪያጅ እንጂነር አሸናፊ ሊካሳ በሰጡት ማብራሪያ ግንባታው በመጓተቱ ምክንያት ግንባታውን ይዞ የነበረው ተቋራጭ በአዲስ እንዲተካ መደረጉን አንስተዋል። አሁን ላይም ግድቡን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ ሁሉን አቀፍ ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። የውሃ መስኖ መቆጣጠሪያው ሲቪል ስራ ሙሉ በሙሉ መጠናቀቁን ጠቁመው፤ የኤሌክትሮ መካኒካል ስራው በሂደት ላይ መሆኑን ገልጸዋል። ግድቡ በአሁኑ ወቅት ውሃ መያዝ መጀመሩን ጠቅሰው፤ እስካሁን 33 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃ መያዙንም ተናግረዋል። የግድቡ ግንባታ 94 በመቶ መድረሱን ጠቁመው፤ የግዱቡ የውሃ ማስተንፈሻ ስፒልዌይ ስራም መጠናቀቁን ገልጸዋል። የግድቡ ግንባታ መሉ በሙሉ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር በርካታ ነዋሪዎችን በመስኖ ልማትና በመጠጥ ውሃ ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ተናግረዋል።
የደባርቅን የመልማት ፀጋ ወደ ተጨባጭ አቅም ለመቀየር ከተማዋን በመሰረተ ልማት ማበልጸግ ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Aug 24, 2026 375
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦የደባርቅን የመልማት ፀጋ ወደ ተጨባጭ አቅም ለመቀየር ከተማዋን በመሰረተ ልማት ማበልጸግ እንደሚገባ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። የደባርቅን ከተማ ለማልማት የተዘጋጀ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር "ደባርቅን እናሳምር ከተማችንን እናድምቅ" በሚል መሪ ሀሳብ በሂልተን ሆቴል እየተካሄደ ይገኛል። በመርሃ ግብሩ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች እና ባለሀብቶች ተገኝተዋል። በገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብሩ "ኑ ተፈጥሮ የገለጠችውን ድንቅ የቱሪስት መስህብ የስሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ መግቢያ በር የሆነችውን ደባርቅ ከተማ በጋራ እናልማ" የሚል ጥሪ ቀርቧል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ደባርቅ የስሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ መግቢያ ከተማ ናት። ይሁን እንጂ ደባርቅ የታሪክ ባለቤትነቷን፣ የቱሪዝም መተላለፊያነቷን የሚመጥን ልማት አልታደለችም ብለዋል። የደባርቅን የመልማት ፀጋ ወደ ተጨባጭ አቅም መለወጥ የሚያስችል እንቅስቃሴ መጀመሩንም ጨምረው ገልጸዋል። በመሆኑም ከተማዋን በማልማት የተፈጥሮ ውበቷን ለመግለጥ ሁሉም በጋራ ትብብር ሊያደርግ ይገባል ብለዋል። የደባርቅ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ከንቲባ ጌትነት ፀጋየ በበኩላቸው፤ ደባርቅ የቀድሞ የሰሜን አውራጃ ከተማ፣ በዓለም ቅርስነት የተመዘገበው የስሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ መገኛ የቱሪዝም ቀዬ መሆኗን ገልጸዋል። ደባርቅ በተፈጥሮ ሀብቶች የበለጸገች የቱሪዝም ማዕከል ብትሆንም የሚገባትን ያህል መልማት ባለመቻሏ የቱሪስቶችን የቆይታ ጊዜ ማራዘም አልቻለችም ነው ያሉት። ስለሆነም መንግሥት ያመጣው የኮሪደር ልማት ተቋዳሽ እንድትሆን ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።  
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች የሕዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጡ ነው
Aug 24, 2026 151
ሳውላ፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በመደመር መንግስት እሳቤ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የህዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጡ መሆናቸውን የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ ገለጹ። አቶ ገብረመስቀል ጫላን ጨምሮ ከክልሉና ከዞኖች የመጡ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች በጎፋ ዞን እና በሳውላ ከተማ በመደመር መንግስት እሳቤ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎችን ተመልክተዋል።   አቶ ገብረመስቀል በወቅቱ እንደገለጹት በክልሉ በመደመር መንግስት እሳቤ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የህዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጡ ነው። በክልሉ ጎፋ ዞንም በግብርናና በኮሪደር ልማት የተከናወኑ ተግባራት የዜጎችን ተጠቃሚነት ያሳደጉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በእንስሳት እና በዶሮ እርባታ ዘርፍ እየተተገበሩ ያሉ ሥራዎች ውጤታማ ናቸው ያሉት አቶ ገብረመስቀል፣ በዘርፉ የተሰማሩ ዜጎችም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በተለይ በሳውላ ከተማ በወተት እና በወተት ተዋጽኦ ምርት ላይ የተሰማሩ ወጣቶች ካፒታላቸውን ከ64 ሺህ ብር መነሻ ወደ 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ማሳደገቻው ለሌሎች ተሞክሮ ይሆናል ብለዋል። በክልሉ ለሚያጋጥሙ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችም በራስ አቅም ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን አቶ ገብረመስቀል አያይዘው ጠቅስዋል።   በተለይም ካለፈው በጀት ዓመት ጀምሮ ሀብት የማሰባሰብና ሰብል የማምረት ሥራው ተጠናክሮ እየተከናወነ መሆኑን ነው የገለጹት። በጎፋ ዞን ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የልማት ሥራዎች ውጤት ተመዝግቧል ያሉት ደግሞ የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ ናቸው።   ተደራጅተው በሌማት ትሩፋት መርሀግብር ወደሥራ የገቡ ወጣቶች ከራሳቸው ባለፈ ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻላቸውን ገልጸዋል። በዞኑ በተለይ በዶሮ እርባታ፣ በማር ምርት፣ በወተት ልማትና በሌሎችም ዘርፎች የመጣውን ውጤት ለማስቀጠል ልዩ ትኩረት መሰጠቱንም ጠቁመዋል። ከሦስት ዓመት በፊት በ64 ሺህ ብር መነሻ ካፕታል የአንድ ቀን የዶሮ ጫጩቶችን እርባታ ሥራ እንደጀመሩ የተናገረው ደግሞ ወጣት ሰላሙ ዮናስ ነው።   በሂደት ሥራቸውን ወደ ወተት ላም እርባታ ሥራ እንደቀየሩ ገልጾ በአሁኑ ወቅትም ለሳውላ ከተማ ነዋሪዎች የወተት ምርታቸውን በስፋት እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግሯል። የወተት ላሞቻቸው ቁጥር ከ8 በላይመድረሱን የገለጸው ወጣት ሰላሙ፣ ካፒታላቸውም ከ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ መድረሱንና ለአምስት ሰዎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም አስረድቷል። ሥራቸውን በማስፋፋት ይበልጥ ውጤታማ ለመሆንም የእንስሳት መኖ ልማት ሥራ እንደጀመሩ ጠቁሞ፣ በመንግስት እየተደረገላቸው ያለ ድጋፍ ለውጤታማነታቸው አጋዥ በመሆኑ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቋል።  
ኢትዮጵያ በሆርቲካልቸር ዘርፍ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብት ምቹ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት አቅም አላት - የሕንድ ባለሀብት ጋጄንድራ ሲንግ
Aug 24, 2026 188
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በአትክልትና ፍራፍሬ የግብርና ልማት ዘርፍ ዓለም አቀፍ የገበያ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብት ምቹ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት አቅም እንዳላት በግብርና ኢንቨስትመንት የተሰማሩት የሕንድ ባለሀብት ጋጄንድራ ሲንግ ገለጹ። ጋጄንድራ ሲንግ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወላይታ ዞን ቦዲቲ አካባቢ በአቮካዶ ልማት ተሰማርተው እየሰሩ ይገኛሉ። በግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፍም በበርካታ ሀገራት የገበያ ጥናት በማካሄድ ለሆርቲካልቸር ዘርፍ ባላት ምቹ የተፈጥሮ ሁኔታና ጠንካራ የመንግሥት ድጋፍ ምክንያት ኢትዮጵያን መምረጣቸውን ተናግረዋል። በዚህም በኢትዮጵያ የተፈጠረውን ምቹ የግብርና ኢንቨስትመንት ምኅዳር መሰረት ያደረገ የአዋጭነት ጥናት በማካሄድ በፍራፍሬ ልማት ዘርፍ ተሰማርተው እየሰሩ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ በተለይም በሆርቲካልቸር ዘርፍ ያላት ከፍተኛ የመልማት አቅም በመጠቀም ባለሀብቶች መዋዕለ ንዋያቸውን ፈሰስ በማድረግ የሚጠቀሙበት ዕድል የተፈጠረባት ሀገር መሆኗን አንስተዋል። በኢትዮጵያ ካለው የሀገር ውስጥ ገበያ ባለፈ በአትክልትና ፍራፍሬ ዘርፍ በዓለም አቀፍ ገበያ ምርቶችን ማቅረብ የሚያስችል የልማት ከባቢ መፈጠሩንም አስገንዝበዋል። መንግሥት በግብርና ዘርፍ ለተሰማሩ አርሶ አደሮች ድጋፍ እያደረገ ነው ያሉት ጋጄንድራ፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ለኢንቨስትመንት የሰጠው ቁርጠኝነትም ምቹ የልማት ምኅዳር ፈጥሯል ብለዋል። በአዲስ አበባ እየተሠራ ያለው ሥራ የከተማዋን ገጽታ ከማሻሻል ባሻገር፤ በቢሾፍቱ እየተገነባ ያለው ግዙፍ የአየር ማረፊያ የመንግሥት የልማት ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን ተናግረዋል። መንግሥት በአቮካዶ ምርት ላይ አበረታች ተግባር እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፤ በገበያ ተደራሽነት ላይም እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ አንስተዋል። ኢትዮጵያ በቡና ወጪ ንግድ ያላትን ልምድ በመጠቀም በሆርቲካልቸር ዘርፍ ግንባር ቀደም ላኪ የመሆን ዕድል እንዳላት አንስተዋል።  
በደብረ ብርሃን ከተማ የሚገነባው የደረቅ ወደብ ተርሚናል የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን ለማሳለጥ ወሳኝ ሚና አለው
Aug 24, 2026 152
ደብረ ብርሃን፤ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል ደብረ ብርሃን ከተማ የሚገነባው የደረቅ ወደብ ተርሚናል በክልሉ በፍጥነት እያደገ የመጣውን የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ለማሳለጥ ወሳኝ ሚና እንዳለው ተገለጸ። በጠቅላላው 275 ሚሊዮን ብር ወጪ በደብረ ብርሀን ከተማ ለሚገነባው የደረቅ ወደብ ተርሚናል ዛሬ የመሰረት ድንጋይ በማስቀመጥ የግንባታ ሥራው በይፋ ተጀምሯል።   በማስጀመሪያ መርሀግብሩ ላይ የአማራ ክልል መንገድ፣ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ቢሮ ሃላፊ ጋሻው አወቀ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ የደረቅ ወደብ ግንባታው በክልሉ በፍጥነት እያደገ የመጣውን የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ሥራዎች ለማሳለጥ ያግዛል። በቢሮው ባለቤትነት ዛሬ የመሰረት ድንጋይ ተቀምጦ የግንባታ ሥራው የተጀመረው የደረቅ ወደብ ሲጠናቀቅ የደብረ ብርሀን ከተማና የማህበረሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ያሳድጋል ብለዋል።   ደብረ ብርሃን ከተማ ከጅቡቲ ወደብ እና ከአዲስ አበባ ከተማ ባላት ቅርበት ምክንያት ምርትን በፍጥነት ከውጪ ወደሀገር ውስጥ ለማስገባትና ለማስወጣት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳላት ገልጸዋል። የወደቡ መገንባትም ተመራጭነቷን ይበልጥ ያሳድገዋል ብለዋል።   እንደ ሃላፊው ገለጻ የደረቅ ወደቡ ግንባታ ሥራ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ሲጠናቀቅ በቀን ከ1ሺህ በላይ የጭነት ተሽከርካሪዎችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ በድሉ ውብሸት በበኩላቸው እንዳሉት፣ ከከተማው ፈጣን እድገት ጋር ተያይዞ የደረቅ ጭነት ተሽከርካሪዎች ቁጥር ከጊዜ ወደጊዜ እያደገ ነው።   ለዚህም የደረቅ ወደብ ተርሚናሉ መገንባት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ግንባታው በታቀደለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ከተማ አስተዳደሩ አስፈላጊው እገዛና ትብብር ያደርጋል ብለዋል። በተያያዘ ዜና የሰሜን ሸዋ ዞን መንገድ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መምሪያ ከ75 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጭ ያስገነባው የአሽከርካሪና ተሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ አገልግሎት ማዕከል ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።   በተርሚናል ግንባታ ሥራ ማስጀመሪያ ላይ ከክልሉ፣ ከዞንና ከደብረብርሃን ከተማ አስተዳደር የተውጣጡ የሥራ ሀላፊዎችና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍል ተወካዮች ተገኝተዋል።
በአማራ ክልል በመኸር ወቅቱ ከ3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም እርሻ በዘር ተሸፍኗል
Aug 24, 2026 132
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፡- ‎በአማራ ክልል በመኸር እርሻ ከ3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም መልማቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የሰብል ልማት ባለሙያ ወይዘሮ እንዬ አሰፋ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተያዘው የመኸር ወቅት የሰብል ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ የተሻሻሉ አሰራርና ቴክኖሎጂዎች ጥቅም ላይ እንዲውሉ ተደርጓል። ለዚህም ለአርሶ አደሩ በበቂ መጠን ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ ከማቅረብ ባለፈ በየደረጃው በሚገኙ የግብርና ባለሙያዎች የቅርብ ክትትልና ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮው የመኸር ወቅት በኩታ ገጠም እርሻ ለማልማት ከ 3 ሚሊዮን 338 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማረስ ታቅዶ እየተሰራ ሲሆን እስካሁን በተደረገ ጥረት የእቅዱን 96 በመቶ ማሳካት መቻሉን ተናግረዋል። የተሻሻሉ አሰራሮችን በመጠቀም በቆሎ፣ ስንዴ፣ ማሽላ ጤፍና በቆሎን ጨምሮ በ10 ዋና ዋና ሰብሎች በኩታ ገጠም የለሙ ሲሆን ከዚህ ውስጥም 141 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይሰበሰባል ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል። በኩታ ገጠም ለለማው ሰብል ከ3 ሚሊዮን 329 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያና 212 ሺህ 381 ኩንታል ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ እንደዋለም ባለሙያዋ አስታውቀዋል።    
በኦሮሚያ ክልል ስራ አጥነትን ለመቀነስና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Aug 24, 2026 176
አዳማ ፤ነሐሴ 18/2018(ኢዜአ )፡-በኦሮሚያ ክልል ስራ አጥነትን ለመቀነስና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ በክህሎት ልማት ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን የክልሉ የስራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ። በኦሮሚያ ክልል ያለውን ከፍተኛ የወጣቶች ቁጥርና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የስራ ፈላጊዎች መጠን ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ዘላቂ የስራ ዕድል መፍጠር የክልሉ መንግስት ዋነኛ ትኩረት ሆኖ ቆይቷል።   ቀደም ሲል የሚደረጉ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎችና የስራ ዕድል ፈጠራ ጥረቶች በቂ የቴክኒክና የክህሎት ክፍተት ባለባቸው ስራ ፈላጊዎች ምክንያት የተፈለገውን ያህል ውጤት ሲያመጡ አልታዩም። በዚህም ምክንያት የክልሉ የስራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ ችግሩን ለመፍታት የሙያና ክህሎት ስልጠናዎችን እንደ ዋነኛ መሳሪያ በመጠቀም፣ ከመንግስታዊና መንግስታዊ ካልሆኑ ባለድርሻ አካላት ጋር የተቀናጀ አሰራር በመዘርጋት ላይ ይገኛል። ዛሬ በአዳማ ከተማ እየተካሄደ የሚገኘው የምክክር መድረክም፣ ቢሮው ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት ዜጎችን በሙያና ክህሎት ለማብቃት የሚያደርገው የዚሁ ጥረት አካል ነው።   የቢሮው ሃላፊ ኢንጂነር ኤባ ገርባ በወቅቱ፤ ስራ አጥነትን ከመሰረቱ ለመቀነስ፣ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ተኪ ምርት ለማምረት በሙያ የበቃ የሰው ሃይል በጥራትና በብዛት ማፍራት ወሳኝ ነው ብለዋል። የክልሉ ዜጎች በሙያ ራሳቸውን ችለው ከመደበኛ ስራ በተጨማሪ በክህሎትና ኢንተርፕሩነርሽፕ ራሳቸውን ማጎልበት አለባቸው ብለዋል። ገበያው የሚፈልገውን የሰው ሃይልና የሙያ ልማት ላይ መስራት ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከግብርና፣ ትምህርት ፣ ማዕድን፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂን ጨምሮ ከተለያዩ ሴክተሮች ጋር በጋራ እየሰራን ነው ብለዋል። የቢሮው የክህሎት ልማት ዘርፍ ሃላፊ አቶ ነርሰዲን ቃድ በበኩላቸው የክህሎት ልማቱ መነሻ ገበያ ተኮር ሙያተኞችን ማፍራት ነው ብለዋል።   በየአካባቢው ያሉ ፀጋዎችንና አቅሞችን በመለየት የልማት ፕሮጄክቶች፣ ሆቴሎችና የቱሪዝም መስቦች እንዲሁም የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ ትኩረት አድርገን አጫጭር የሙያ ስልጠና እንሰጣለን ነው ያሉት። በአዲሱ በጀት ዓመት ሰፊ የስራ ዕድል ለመፍጠር የሚያስችሉ ገበያ ተኮር አጫጭር የሙያና ክህሎት ልማት ስልጠናዎች 3 ሚሊዮን ለሚሆኑ ዜጎች በመስጠት ወደ ስራ ለማስገባት መታቀዱን ለአብነት አንስተዋል። ለዚህም በክልሉ 21 ዞኖችና 23 ከተሞች ያሉትን ፀጋዎችና የገበያ ፍላጎቶችን በመለየት የክህሎት ልማት ስልጠና ይሰጣል ብለዋል።   በኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ የሁለተኛ ደረጃ የትምህርት ፕሮግራሞች ዳይሬክተር እጩ ዶክተር መንግስቱ ለታ እንደገለፁት በሙያና ክህሎት የዳበረ የሰው ሃይል ለማፍራት ከስራና ክህሎት ቢሮ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመን አብረን እየሰራን ነው ብለዋል። "በአሁኑ ወቅት ለ7ኛ እና 8ኛ ክፍል ተማሪዎች የክህሎት ትምህርት እየተሰጠ ይገኛል" ያሉት ዳይሬክተሩ ለ11ኛ እና 12ኛ ክፍል ተማሪዎችም የሙያ ትምህርት ለመስጠት 23 የሙያ አይነቶች ተለይተው መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Aug 24, 2026 140
ሚዛን አማን፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ):በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸምና የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በሚዛን አማን ከተማ እያካሔደ ነው።   የቢሮው ኃላፊ አቶ ታሪኩ አካሉ በመድረኩ ላይ እንዳሉት፣ የንግድ ሚዛን ሥርዓትን በማስጠበቅ ጤናማ ግብይት መፍጠር ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ ይገኛል። በዚህም በተጠናቀቀው የ2018 የበጀት ዓመት የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ተግባራት የተከናወኑ ሲሆን ይህም ውጤታማ እንደነበር ተናግረዋል። ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመከላከል በተደረገው የክትትልና የቁጥጥር ሥራ 8 ሺህ በሚሆኑ ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን ገልጸዋል። ሕገ-ወጥ ንግድ የኑሮ ውድነትን የሚያባብስ መሆኑን ጠቅሰው፣ በተግባሩ ላይ በተገኙ ነጋዴዎች ላይ በተወሰደው እርምጃ ከ52 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር በላይ ወደ መንግሥት ካዝና ገቢ ማድረግ እንደተቻለ አቶ ታሪኩ ጠቅሰዋል። በሌላ በኩል የቅዳሜና እሑድ ገበያ ማዕከላትን በማስፋፋት ኑሮን ለማረጋጋት ያለውን አቅም ከግምት ውስጥ በማስገባት ወደ 36 ከፍ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል።   የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ኢንዱስትሪና ንግድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጌታቸው መለሰ፣ ከተማ አስተዳደሩ ከ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት በመመደብ የቅዳሜና እሑድ ገበያ ማዕከላትን ማደራጀት መቻሉን ገልጸዋል። የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ በመንግሥት የተነደፉ ኢንሼቲቮችን በአግባቡ መሬት ላይ በማውረድ ሸማቹን ከአላስፈላጊ የዋጋ ጭማሪ መታደግ ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል።   በምዕራብ ኦሞ ዞን የጀሙ ከተማ አስተዳደር ንግድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ በረከት ደምሴ በበኩላቸው፣ በከተማዋ ያሉ ሁለት የግብይት ማዕከላትን ለማስፋፋት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በማዕከላቱ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት ምርት የማቅረብ ሥራ እየተሠራ ሲሆን፣ የዋጋና ምርት መደበቅ ሕገ-ወጥ ተግባራት ላይ ጠንካራ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
ለገበያው መረጋጋት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ የሚገኙት የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች
Aug 24, 2026 114
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብና ገበያን በማረጋጋት ጉልህ ጠቀሜታ እያስገኙ መሆኑን ሸማቾችና ምርት አቅራቢዎች ገለጹ። መንግሥት ገበያውን ለማረጋጋት ከወሰዳቸው እርምጃዎች መካከል የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ማደራጀት አንዱ ሲሆን፣ መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ ማኅበረሰብ እንዲደርሱ እያስቻለ ነው። ገበያዎቹ አርሶ አደሮችና አነስተኛ አምራቾች ከደላላ ጣልቃ ገብነት ነፃ ሆነው ምርቶቻቸውን በቀጥታ ለተጠቃሚው እንዲያቀርቡ በማስቻል የገበያ ትስስርን አጠናክረዋል። ይህም ለአምራቾች የተሻለ ገቢ እንዲፈጠር፣ ለተጠቃሚዎች ደግሞ መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ በማድረግ የገበያ መረጋጋትን እያጎለበተ ይገኛል። ኢዜአ በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ሲሸምቱ ያነጋገራቸው ሸማቾች እንደገለጹት፣ ገበያዎቹ መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶችን በዓይነት፣ በጥራትና በተመጣጣኝ ዋጋ በአቅራቢያቸው ማግኘት አስችለዋቸዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወይዘሮ ሶስና ገብረሚካኤል እንዳሉት፤ ገበያው በአቅራቢያቸው መከፈቱ ቀደም ሲል መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶችን ለመሸመት ይባክን የነበረውን ጊዜ፣ ጉልበትና ወጪ ቀንሷል። "አሁን የቅዳሜና እሁድ ገበያው በአቅራቢያችን በመኖሩ መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት ችያለሁ" ብለዋል። መንግሥት በየአካባቢው ያስጀመራቸው የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች እንግልትንና ወጪን በመቀነስ፣ የኑሮ ውድነትን ለማስታገስና ገበያን ለማረጋጋት የወሰደው ወሳኝ እርምጃ መሆኑንም ጠቁመዋል። በቀጣይም መንግሥት የሰብልና መሰል ምርቶችን በብዛትና በጥራት በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች እንዲቀርቡ በማድረግ፣ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ተጠቃሚ የማድረግ ተግባሩን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ ዝናሽ ወጋየው፤ በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የሚቀርቡ መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶች ጥራት ያላቸውና ከመደበኛው ገበያ ከ20 በመቶ በላይ ቅናሽ ያላቸው መሆናቸውን ተናግረዋል። መሰል ገበያዎች ለሸማቾች በቅርብ ከመገኘታቸው ባለፈ፣ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት የሚያስችሉ በመሆናቸው መጠናከር እንደሚገባቸው ገልጸዋል። የቅዳሜና እሁድ ገበያዎቹ የሸማቾችን ጊዜ፣ ጉልበትና ወጪ በመቆጠብ በኩል ከፍተኛ አስተዋጽኦ ከማበርከታቸው ባለፈ ለዋጋ ንረት መረጋጋት ዓይነተኛ መፍትሔ መሆናቸውን አክለዋል። በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የፍጆታ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ መቅረባቸው ለማኅበረሰቡ እፎይታ እየሰጠና የኑሮ ውድነትን እያረጋጋ እንደሚገኝ የተናገሩት ደግሞ ወይዘሮ ቃልኪዳን ሰለሞን ናቸው። ገበያዎቹ በየዕለቱ የምንጠቀምባቸውን መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶች በአቅራቢያችን እንድናገኝ አስችለውናል ሲሉም ገልጸዋል። በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ምርቶችን ለሽያጭ ይዘው ከቀረቡት መካከል ወጣት ሄኖክ ተሰማ፤ ምርቶችን በቀጥታ ከማሳ በማምጣት በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቾች እያቀረቡ እንደሚገኝ ገልጿል። አንዋር ሰዒድ በበኩላቸው፤ በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የሚገበዩ ሸማቾች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ በመምጣቱ ምርቶቻቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል።
በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ውጤታማ ናቸው
Aug 23, 2026 261
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 17/2018 (ኢዜአ)፡- በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር በቅንጅት የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ውጤት ማምጣታቸውን የከተማዋ ተቀዳሚ ምክተል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተከናወኑ የመንግስትና የፓርቲ ስራዎችን አፈጻጸም በመገምገም ላይ ይገኛል።   በመድረኩ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው እንደገለጹት፣ የከተማዋን ሰላምና ልማት ዘላቂ ለማድረግ በቅንጅት የተከናወኑ ተግባራት ውጤት አምጥተዋል። በፖለቲካው ዘርፍም የመደመር መንግስት እሳቤዎችን መሰረት በማድረግ፣ አሰባሳቢ ትርክት የመገንባትና አሳታፊ የፖለቲካ መስመሮች መዘርጋታቸውን ጠቁመዋል። ለአብነትም በ7ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ህዝቡን በነቂስ ወጥቶ ይበጀኛል ያለውን መንግስት በመምረጥ ሀገርን ማስቀደሙን አሳይቷል ብለዋል። ማህበራዊ ልማትን በማፋጠን ረገድም በትምህርት፣ በጤና እና የስራ አጥነት ችግርን በመፍታት ላይ ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውን አቶ ጎሹ አመላክተዋል። በከተማዋ ነዋሪዎች የቤት ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ለመስጠትም የቤት መስሪያ ቦታ መሰጠቱን አንስተዋል። የከተማዋን ገቢ ለማሳደግ የሚሰሩ የልማት ስራዎች፣ የቱሪዝም መዳረሻዎች እንዲሁም የኮሪደር እና የጣና ዳር ልማት ፕሮጀክቶች በተሳካ ሁኔታ መከናወናቸውን ገልጸዋል። በከተማዋ የተመዘገቡትን ልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን ለማስቀጠል ቅንጅታዊ ተግባራት በቀጣይም እንደሚጠናከር ገልጸዋል። በመድረኩ በየደረጃው ያሉ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።  
ከህዳሴ ግድብ እስከ ግዙፍ የአውሮፕላን ማረፊያ - የኢትዮጵያ አህጉራዊ የመሰረተ ልማት መሪነት
Aug 21, 2026 978
(በሙሴ መለሰ) መሰረተ ልማት የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ማዕዘን ከሆኑ ቁልፍ ዘርፎች መካከል የሚጠቀስ ነው። ኢትዮጵያ የነገ ብልጽግናዋን እውን ለማድረግና የዜጎቿን ፍትሀዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተፋጠነ መልኩ እየተገበረቻቸው የሚገኙት ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ቁልፍ ሚና አላቸው ። በመንገድ፣ በባቡር፣ በኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ የኮሪደር ልማት እና ሌሎች ግንባታዎች ላይ እያፈሰሰች ያለው መዋዕለ ንዋይ ኢትዮጵያን እና ህዝቦቿን የሚመጥን የኢኮኖሚ እድገት እና የአኗኗር ዘይቤን በመፍጠር ረገድ ያላቸው አስተዋጽኦም ቀላል አይደለም። ግዙፉ ፕሮጀክቶቿ መካከልም በጳጉሜን ወር 2017 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለአፍሪካ የኢነርጂ ትስስር ውጥን ትልቅ የምስራች ሆኖ መጥቷል። የጎረቤት ሀገራት ከግድቡ የሚያገኙት የኤሌክትሪክ አቅርቦት ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከር ያስችላል። በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኙ የሀገራት መሪዎች ባደረጉት ንግግርም በአጽንኦት ያረጋገጡት የህዳሴ ግድብ የአፍሪካ የራስን የመቻል ምልክት እና የኢትዮጵያን አይበገሬነት ተምሳሌትነት ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በህዳሴ ግድብ ምርቃት ወቅት የተለያዩ ግዙፍ መሰረተ ልማቶች ግንባታ እንደሚጀመር ይፋ አድርገዋል። የኒውክሌር ኃይል ማበልጸጊያ፣ የጋዝ ፋብሪካ ማስመረቅ፣ የነዳጅ ማጣሪያ እውን ማድረግ፣ በአፍሪካ ግዙፉ አየር ማረፊያ የሆነውን የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ መጀመር፣ ሁለተኛውን የጋዝ ፋብሪካ ግንባታ ማስጀመር፣ የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ ማስጀመር እና የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶች በመላው ሀገሪቱ ማስጀመር በጠቅላይ ሚኒስትሩ ይፋ የተደረጉ ፕሮጀክቶች/የጉባ ብስራቶች/ ናቸው። በሶማሌ ክልል የጋዝ ፋብሪካ የተመረቀ ሲሆን፣ በአፍሪካ ታሪክ በትልቅነቱ ቀዳሚ የሆነው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በግንባታ ሂደት ላይ ይገኛል። ይህ ግዙፍ የአየር ማረፊያ ፕሮጀክት የሀገሪቱን የሎጂስቲክስና የቱሪዝም አቅም ከመቀየር ባለፈ፣ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ያላትን የአቪዬሽን መሪነት ይበልጥ የሚያጠናክር ነው። ከዚህ ጋር ተያይዞ የሀገሪቱን የግብርና ምርታማነት በዘላቂነት ለመደገፍ ወሳኝ የሆነው የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ እና የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶች ግንባታ በየክልሎቹ ካሉ የከተማ ማዘመንና የኮሪደር ልማት ስራዎች ጋር በተቀናጀ መልኩ ወደ ተግባር እየተሸጋገረ ይገኛል። በግንባታ ላይ የሚገኘው የኮይሻ የኤሌክትሪክ ኃይል ግንባታም ለኢነርጂ አቅርቦት እድገት የበኩሉን ሚና የሚጫወት ሲሆን፣ ሀገሪቱ የጀመረችውን የአረንጓዴ ኢነርጂና የኢንዱስትሪ ልማት ጉዞ በከፍተኛ ደረጃ ያፋጥነዋል። እነዚህ ግዙፍ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ሀገሪቱ በቅርቡ ከጀመረችው አጠቃላይ የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የገበያ መር ሥርዓት ጋር የተቆራኙ ስትራቴጂካዊ እርምጃዎች ተደርገው ይወሰዳሉ። የሀገር ውስጥ ምርታማነትንና የዜጎችን የኑሮ ጥራት ከመሰረቱ የሚያሻሽሉ ከመሆናቸውም በላይ፣ ሀገሪቱ በውጭ ዕርዳታና ብድር ላይ ከመደገፍ ወጥታ በሀገር ውስጥ እቅድና አቅም ላይ ተመስርታ የራሷን ዕድል የምትወስን አይበገሬነቷን በተግባር ያሳዩ የኩራት መገለጫዎች ናቸው። መንግሥት በነዳጅ፣ በጋዝ፣ በማዳበሪያ እና በ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶች ግንባታ ላይ የጀመራቸው ግዙፍ ፕሮጀክቶች ቀደም ሲል የነበረውን የመንግሥትን ብቻ ፋይናንስ ጥገኝነት በመቀነስ፣ የሀገር ውስጥ እና የውጭ የግል ባለሀብቶችን (Private Sector) በከፍተኛ ደረጃ የሚያሳትፉ አዳዲስ የአጋርነት ሞዴሎችን የፈጠሩ ናቸው። የተቀናጁ መሰረተ ልማቶች ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያለውን የንግድና የኢኮኖሚ ትስስር በማላቅ ቀጣናዊ ትብብርን ወደ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ በመሆናቸው፣ ኢትዮጵያ በአህጉራዊ ትስስርና በአፍሪካ የነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነቶች ውስጥ ያላትን ተወዳዳሪነትና ተጠቃሚነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያሳድጉት አያጠራጥርም። በመሆኑም እነዚህን ስትራቴጂካዊ የካፒታል ፕሮጀክቶች ከተጀመሩት የከተማ ማዘመንና የኮሪደር ልማት ስራዎች ጋር መተሳሰር፣ ኢትዮጵያን የአፍሪካ የብልፅግና ተምሳሌትና የኢኮኖሚ ማዕከል አድርጎ ለመገንባት ለተቀመጠው የረጅም ጊዜ ሀገራዊ ራዕይ መሳካት አስተማማኝ ዋስትና ተደርገው ይወሰዳሉ። የመደመር መንግሥት የኢትዮጵያዊያንን የእድገት መሻት ለማሳካት የሚያከናውነው የተቀናጀ ስራ ተጠናክሮ የሚቀጥል ነው። ለዚህ ስኬት ደግሞ ሁሉም ዜጋ እጅ ለእጅ ተያይዞ በጋራ መንቀሳቀስ ይኖርበታል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመደመር መንግሥት መጽሐፋቸው ገጽ 221 ላይ እንዳመለከቱት አይበገሬነት አንድ አካል ለብቻው የሚወጣው ጉዳይ አይደለም ። ከብዙዎች ጋር ተደምረን የጋራ ጉዳይ መሆኑን ተግባብተን በመደጋገፍና በመተባበር የምንወጣው ጉዳይ ነው።
የኢትዮ-ቻይና ስትራቴጂካዊ አጋርነት ለቻይና-አፍሪካ ትብብር ትልቅ ተምሳሌት ነው - አምባሳደር ቼን ሃይ
Aug 21, 2026 535
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያና ቻይና በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂካዊ አጋርነት፣ በቻይና እና አፍሪካ መካከል የጋራ ተጠቃሚነትን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ እንደሚገኝ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ ገለጹ። ሁለንተናዊ ስትራቴጂካዊ ግንኙነቱ ቻይና እና ኢትዮጵያ በሁሉም አጋጣሚዎች አብረው የሚቆሙበትና በጋራ የሚሰሩበት ማዕቀፍ መሆኑን አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ወደ ሁለንተናዊ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ከፍ ማለቱ፣ የዓለም አቀፍ ትብብርንና የጋራ ዕድገት አቅም የሚያንጸባርቅ ከመሆኑም በላይ ለቻይና እና አፍሪካ ግንኙነት መጠናከር እንደ ዋና መሠረት እንደሚያገለግልም ተናግረዋል። ግንኙነቱ ከተለመደው የዲፕሎማሲ ወሰን በመሻገር፣ በጽኑ ፖለቲካዊ እምነትና በጠንካራ ወዳጅነት ላይ ወደተመሰረተ ሁለገብ አጋርነት ማደጉን አመልክተዋል። በሁለቱ ሀገራት መሪዎች ጥበበኛ አመራር የሁለትዮሽ አጋርነቱ በበርካታ ዘርፎች ጉልህ ውጤት እየተመዘገበበት መምጣቱንም ነው የገለጹት። በቅርብ ዓመታት በሁለቱ ሀገራት መሪዎች መመሪያ አማካኝነት ቻይና እና ኢትዮጵያ በፖለቲካውና በኢኮኖሚ ዘርፍ በጋራ እየሰሩ ነው ብለዋል። የሁለቱን ሀገራት ሕዝቦች ተጠቃሚነት ለማረጋገጥም ይበልጥ ትብብራቸውን እያጠናከሩ መሆኑን አንስተዋል። ሁለቱ ሀገራት የደቡብ ንፍቀ ዓለም (Global South) ድምፅ መሆናቸውን ገልጸው በብሪክስ (BRICS) ማዕቀፍ ውስጥ የነቃ ተሳትፎ እያደረጉ እንደሚገኝም አመልክተዋል። በነዚህ መድረኮች አማካኝነት ቻይና እና ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ የጠበቀ ትብብር እንዳላቸው ጠቅሰው፤ ፍትሃዊ የዓለም ስርዓት እንዲሰፍንም በጋራ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። ይህ አጋርነት በረጅም ዘመን ታሪካዊ ወዳጅነት ላይ የተገነባ መሆኑን የጠቀሱት አምባሳደሩ፤ አሁን ላይ የዘመኑን ጥያቄዎች በሚመልስ ፈጣን የእድገት ምዕራፍ ውስጥ እንደሚገኝ አብራርተዋል። በአዲሱ ዘመን ሁለንተናዊ ስትራቴጂካዊ አጋርነቱ በከፍተኛ ፍጥነት እንደሚያድግና በጋራ እጣ ፈንታ ላይ የተመሰረተ የቻይና እና አፍሪካ ወዳጅነትን የመገንባት ውጥን ስኬታማ እንደሚሆን ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እና ቻይና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1970 መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። የሀገራቱ የሁለትዮሽ ትብብር በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂካዊ አጋርነት የተሸጋገረው እ.አ.አ በ2023 ነበር። የሀገራቱ ግንኙነት ወደዚህ ከፍተኛ የዲፕሎማሲ ደረጃ ማደጉ ይፋ የተደረገው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቤጂንግ ከተካሄደው ሶስተኛው የቤልት ኤንድ ሮድ (Belt and Road) ጉባኤ ጎን ለጎን ወቅት ከቻይናው ፕሬዚዳንት ሺ ጂንፒንግ ጋር ባደረጉት ውይይት ላይ ነው።
ኢትዮጵያ የግብርና ምርቷን ለማሳደግ በዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ላይ በትኩረት እየሰራች ነው
Aug 21, 2026 320
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ የግብርና ልማትን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ በመስኖ ልማት፣ በተሻሻሉ ምርጥ ዘሮችና በግብርና ሜካናይዜሽን ላይ በትኩረት እየሰራች መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ ገለጹ። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለስልጣን (ኢጋድ) አባል ሀገራት አምባሳደሮች ኮሚቴና የኢጋድ ፓርላማ ፎረም በአግሪፉድ ሲስተም ዙሪያ በአዲስ አበባ ያዘጋጁት ከፍተኛ የልምድ ልውውጥ መድረክ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ እንደገለጹት ኢትዮጵያ የግብርና ልማትን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ በመስኖ ልማት፣ በተሻሻሉ ምርጥ ዘሮችና በግብርና ሜካናይዜሽን ላይ በትኩረት እየሰራች ነው። የክላስተር እርሻ ልማት አርሶ አደሮች የግብዓት፣ የቴክኖሎጂ፣ የባለሙያ ምክክር አገልግሎትና የገበያ ትስስሮችን በተሻለ ሁኔታ እንዲያገኙ እያስቻለ መሆኑን ጠቁመዋል። በተጨማሪም በአረንጓዴ ዐሻራ እና በሌማት ትሩፋት ተነሳሽነቶች የአካባቢ ጥበቃን፣ የግብርና ምርታማነትንና የቤተሰብ ምግብና የአመጋገብ ስርዓትን ለማሻሻል ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። የኢጋድ ዋና ጸሐፊ ተወካይና በድርጅቱ የውጭ አገልግሎት ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር ኦማር ጃማ የአግሪፉድ ሲስተም ለውጥ የካምፓላ የግብርና ልማት ቃል ኪዳንን ወደ ተግባር በማሸጋገር፣ በጠንካራ ፖሊሲ፣ የሕግ ማዕቀፍ፣ በጀትና ኢንቨስትመንት በመደገፍ እንደሚሳካ ጠቁመዋል። ሀገራቱ ለምግብ ዋስትና ችግር፣ ለአየር ንብረት ለውጥ፣ ለዝቅተኛ ምርታማነትና ለውስን የገበያ ትስስር የተጋለጡ በመሆኑ፣ የግብርና ለውጥን ለማፋጠን አባል ሀገራት የተቀናጀ ቀጣናዊ ትብብርን ማጠናከር ይገባቸዋል ብለዋል። በመድረኩ የአግሪፉድ ሲስተም ልማትን ለማፋጠን የፖሊሲ ቅንጅትን፣ የግብርና ኢንቨስትመንትን፣ የቀጣናዊ ንግድ ትስስርንና የፓርላማ ክትትልን ማጠናከል በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ውይይት እየተካሄደ ይገኛል።
አረንጓዴ አሻራ ከአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ጋር መቀናጀቱ ውጤታማ አድርጎናል-አርሶ አደሮች
Aug 21, 2026 214
ገንዳውሃ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ከአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ጋር በማቀናጀት ተጠቃሚ መሆናቸውን የዞኑ አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የቆላ ፍራፍሬ ልማትን በኩታ ገጠም እርሻ ለማልማት ትኩረት ተሰጥቶ እየተከናወነ ይገኛል። በልማቱ ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል አርሶ አደር ደሴ ባይተኩስ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ከአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ጋር አስተሳስረው በመስራታቸው አመርቂ ውጤት አግኝተዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ያለሙትን ሙዝና ማንጎ ለገበያ በማቅረብ ከ150 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ነው የሚናገሩት። በተለይ "በክላስተር መደራጀታችን የውሃ አጠቃቀማችንን እና የግብዓት አቅርቦት ችግራችንን አቃልሎልናል" ያሉት አርሶ አደሩ፣ በዘንድሮው ዓመትም የተሻለ ምርት ለማግኘት እየሰሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሌላኛዋ የወረዳው ነዋሪ አርሶ አደር ፀጋነሽ ብዙነህ በበኩላቸው፥ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተግባራዊ መደረጉ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት በስፋት ለመሳተፍና ተጠቃሚ ለመሆን የሚያስችል ዕድል ይዞ መምጣቱን ገልጸዋል። ሁለት ሄክታር በሚጠጋ መሬት ካለሙት ሙዝ፣ ማንጎና ፓፓያ ከእለት ፍጆታ በተጨማሪ ለገበያ የሚተርፍ ምርት በማምረት ከ100 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ገልጸዋል። የምዕራብ ጎንደር ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ እንዳሉት፥ በዞኑ በ1 ሺህ 113 ሄክታር መሬት ላይ የቡናና የቆላ ፍራፍሬ ልማት እየተካሄደ ይገኛል። ከዚህ ውስጥ 200 ሄክታሩን በክላስተር በፓፓያና በሙዝ ለማልማት በተጀመረው ስራ እስካሁን ከ40 ሄክታር በላይ መሬት መሸፈኑን ገልጸዋል። የፓፓያና የሙዝ ክላስተር ልማትን ይበልጥ ለማስፋፋት መምሪያው ልዩ ትኩረት መስጠቱን የጠቀሱት ኃላፊው፥ አስፈላጊው ግብዓት በወቅቱ ለአርሶ አደሮች እንዲሰራጭ መደረጉን ተናግረዋል።
የማዕድን ዘርፉን የወጪ ንግድ ከማሳደግ ባለፈ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት የመተካቱ ስራ ይጠናከራል
Aug 21, 2026 148
ሃዋሳ ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ) ፦ በበጀት ዓመቱ የማዕድን ዘርፉን የወጪ ንግድ ገቢ ከማሳደግ ባለፈ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት የመተካቱ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የማዕድን ሚኒስቴር አስታወቀ። በማዕድን ሚኒስቴር የማዕድን ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ አቶ ብርሃኔ ያዴሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ከአምስቱ ዋና ዋና የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ ከሆነው የማዕድን ዘርፍ ኢትዮጵያ ተገቢውን ጥቅም እንድታገኝ የተከናወኑ የለውጥ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል። ዘርፉ የሚያስገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ በተደረገ ተቋማዊ ሪፎርም የማዕድን መረጃዎችን በዘመናዊ መልክ በማደራጀት መረጃን መሠረት ያደረገ የማዕድን አመራር ሥርዓት ተዘርግቷል ብለዋል። የማዕድን ፍለጋዎችንና ሳይንሳዊ ሥራዎችን ከማጠናከር ባለፈ፣ ማበረታቻዎችንና ምቹ መደላድሎችን በመፍጠር ዘርፉ የኢኮኖሚው ሞተር እንዲሆን የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውንም ገልጸዋል። በመሆኑም በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመትም በሀገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያ የሆነውን 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር የወጪ ንግድ ገቢ ከማዕድን ማግኘት ተችሏል ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ከወርቅ በተጨማሪ በተመረጡ የማዕድን ዘርፎች ላይ በማተኮር የዘርፉን የወጪ ንግድ ገቢ 6 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ግብ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ወርቅ ላይ ብቻ የተንጠለጠለውን የወጪ ንግድ ገቢ ለማስፋት፣ ዓለም አቀፍ ፍላጎትን መሠረት በማድረግ በጌጣጌጥና በሌሎች የተመረጡ ማዕድናት ላይ በማተኮር ገቢን የማሳደግና ዘላቂነትን የማረጋገጥ ሥራዎች ይከናወናሉ ብለዋል። በተኪ ምርት ረገድም ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ከውጭ የሚገቡ ማዕድናትን በሀገር ውስጥ የመተካት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፣ አንዳንድ ተኪ ምርቶችን ወደ ውጭ የመላክ ዕቅድ የተያዘበት ዓመት መሆኑንም ገልጸዋል። የሲዳማ ክልል ማዕድንና ኢነርጂ ኤጀንሲ ሥራ አስኪያጅ አቶ መስፍን መጩካ በበኩላቸው፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የማዕድናት ልየታ ሥራ በትኩረት መከናወኑን ገልጸዋል።   በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 1 ሺህ 350 ኪሎ ግራም ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ መግባቱንና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ከ11 ሺህ ቶን በላይ ማዕድናት ለማዕከላዊ ገበያ መቅረባቸውን ተናግረዋል። በኮንስትራክሽን ማዕድናትም የሕብረተሰቡን ፍላጎት የሚያሟሉ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካት የሚያስችሉ የማርብልና ግራናይት ማዕድናት ወደ ምርት የማስገባት ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። በክልሉ በጥናት የተለዩ ከ22 በላይ ማዕድናት መኖራቸውን የገለጹት ደግሞ በኤጀንሲው የማዕድን ሀብት ዳይሬክተር ወ/ሮ ምርትነሽ መኮንን ናቸው። ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግም በወርቅ፣ ኮንስትራክሽንና ኢንዱስትሪ ማዕድናት ላይ የተሰማሩ ከ320 በላይ ማኅበራት የገበያ ትስስር እንደተፈጠረላቸው ገልጸዋል። በማርብልና ግራናይት የኢንቨስትመንት ፈቃድ ተሰጥቶ ወደ ምርት ለመግባት የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ከዩናይትድ ኪንግደም ጋር የዓለም ንግድ ድርጅት የሁለትዮሽ ገበያ ዕድል ስምምነት ተፈራረመች
Aug 20, 2026 391
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦​ኢትዮጵያ ከዩናይትድ ኪንግደም ጋር በዓለም ንግድ ድርጅት (WTO) አባልነት ሂደት ማዕቀፍ ስታካሂድ የቆየችውን የሁለትዮሽ የገበያ ዕድል ድርድር በስኬት በማጠናቀቅ የስምምነት ሰነድ ተፈራርማለች። ​የስምምነት ሰነዱን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት ዋና ተደራዳሪ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር እና በኢትዮጵያ የዩናይትድ ኪንግደም አምባሳደር ዳረን ዌልች ተፈራርመውታል። ​በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ይህ ታሪካዊ ስምምነት የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም እና የፖሊሲ ምህዳር ሙሉ በሙሉ ባስጠበቀ መልኩ የተከናወነ ነው ብለዋል። አክለውም ስምምነቱ የሁለቱን ሀገራት የቆየ ዲፕሎማሲያዊ፣ የንግድ እና የኢንቨስትመንት ትስስር ይበልጥ የሚያጠናክር ከመሆኑም በላይ፣ ኢትዮጵያ በዓለም ንግድ ድርጅት ሙሉ አባል ለመሆን የምታደርገውን ጥረት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ወሳኝ ስኬት መሆኑን አብራርተዋል። የዩናይትድ ኪንግደም አምባሳደር ዳረን ዌልች በበኩላቸው፤ የተደረገው ስምምነት የሁለቱን ሀገራት የቆየ የኢኮኖሚና የዲፕሎማሲ ግንኙነት ይበልጥ የሚያጎለብት መሆኑን ገልጸዋል። ዩናይትድ ኪንግደም ኢትዮጵያ ወደ ዓለም ንግድ ድርጅት ለመቀላቀል የምታደርገውን ጥረት እና የምታካሂዳቸውን የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች በሙሉ ቁርጠኝነት መደገፏን የምትቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። ​ኢትዮጵያ እስካሁን ባለው ሂደት ከቻይና፣ ሩሲያ፣ አርጀንቲና፣ ቱርክ፣ ብራዚል፣ ጃፓን፣ ሕንድ፣ ኒውዚላንድ እና ታይላንድ ጋር ተመሳሳይ ስምምነቶችን ተፈራርማለች። ዩናይትድ ኪንግደም ስምምነቱን በይፋ ከፈረሙ አባል ሀገራት 10ኛዋ እና ድርድሩን በስኬት ካጠናቀቁት ደግሞ 11ኛዋ አባል ሀገር ሆናለች።
ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝ ሀብቷን ለማልማት ከማንም ፈቃድ አያስፈልጋትም - የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር)
Aug 20, 2026 343
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝ ሀብቷን የመጠቀም እና የማልማት ሉዓላዊ መብት ስላላት ከማንም አካል ፈቃድ መጠየቅ እንደማያስፈልጋት የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስትሩ አክለውም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ኤሌክትሪክ ኃይል በማመንጨት ለቀጣናው የሚተርፍ ሀብት መሆኑንም አመልክተዋል። ሚኒስትሩ ከፐልስ ኦፍ አፍሪካ (The Pulse of Africa) ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የተገነባው ለኃይል ማመንጨት ብቻ እንደሆነና አዎንታዊ ሚናውን ቀጣናዊ የኤሌክትሪክ ግብይትን በማስፋት ከኢትዮጵያ ድንበር የተሻገረ ጠቀሜታ እንዳለውም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለጎረቤት ሀገራት ማለትም ለጅቡቲ፣ ለኬንያ እና ለሱዳን የኤሌክትሪክ ኃይል በማቅረብ ላይ እንደምትገኝ የጠቆሙት ሚኒስትሩ፣ ከሶማሊያ እና ከደቡብ ሱዳን በኩል ያለው የኢነርጂ ፍላጎት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱንም አብራርተዋል። የዓባይ ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት (CFA) እና የዓባይ ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ የወንዙን የጋራ ጥቅም ለማሳደግ የተደረጉ ጥረቶች ማሳያ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በሌሎች ድንበር ተሻጋሪ የዓለም ወንዞች ላይ ባለው ተሞክሮ ትብብርን የሚጀምሩት የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ቢሆኑም፣ በዓባይ ጉዳይ ግን እንተባበር በማለት ውይይቱን በግንባር ቀደምትነት ስትመራ የቆየችው ኢትዮጵያ መሆኗን አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ከሕዳሴ ግድብ በታች የሚገኙ ሊለሙ የሚችሉ መሬቶቿን ከመስኖ ልማት ውጪ ማድረጓ ለታችኞቹ የተፋሰሱ ሀገራት ያላትን ትልቅ ግምት እንደሚያሳይ ሚኒስትሩ አክለው ገልጸዋል። በቴክኒክ ደረጃ፣ ከግድቡ በታች ከ230 ሺህ ሄክታር በላይ የመስኖ ልማት የሚሆን መሬት አለን፤ ነገር ግን በታችኛው ተፋሰስ በኩል ያለውን ፍላጎት ስለምናውቅ ይህንን አላደረግነውም ሲሉ አስረድተዋል። ሚኒስትሩ የህዳሴ ግድብ ኃይል ካመነጨ በኋላ የሚለቀቀው ውሃ ቀጥታ ወደ ታችኛው ተፋሰስ ወደሚገኙ ወንድም ሀገራት እንደሚፈስ በመግለጽ ኢትዮጵያ ለጋራ ተጠቃሚነት ያላትን ቁርጠኝነት አንስተዋል። ሚኒስትሩ ሕዳሴ ግድብን በጋራ ለማስተዳደር የሚቀርቡ ጥሪዎችን ውድቅ ያደረጉ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ሌሎች ሀገራት በግድቡ ላይ ቁጥጥር የሚደረጉበትን አሰራርን አትቀበልም ብለዋል። በኢትዮጵያውያን ገንዘብ የተገነባውን፣ ኩራታችን እና ብሔራዊ የክብር ፕሮጀክታችን የሆነውን ግድብ፣ ግንባታውን ሲቃወም የነበረ አካል መጥቶ በጋራ እናስተዳድር እንዴት ሊል ይችላል? ሲሉ ጠይቀዋል። ይህ ፈጽሞ የማይቻል፣ በፍፁም ሊታሰብ የማይችል ነው ሲሉም ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የዓባይ ተፋሰስ ሀገራት የኢትዮጵያን የልማት መብት ለመገደብ ከመጣር ይልቅ በውይይት እና በትብብር ላይ ትኩረት ማድረግ አለባቸው የሚል የጸና አቋም እንዳላት ተናግረዋል።
በመዲናዋ የተገነቡ የመዝናኛ ፓርኮች አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን ከዘመናዊ የቱሪዝም መስህቦች ጋር አስተሳስራ እንድትቀጥል አስችለዋታል
Aug 20, 2026 396
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦በመደመር መንግሥት በመዲናዋ የተገነቡት የመዝናኛ ፓርኮች አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን ከዘመናዊ የቱሪዝም መስህቦች ጋር አስተሳስራ እንድትቀጥል ማስቻላቸውን የአንድነት ፓርኮች ኮርፖሬሽን ገለጸ። በመዲናዋ የተገነቡት ፓርኮች ልዩ ልዩ ሁነቶችን ማከናወን የሚያስችሉ መሰረተ ልማቶች የተሟላላቸው እና ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠር ማስቻላቸውም ተመላክቷል። የመደመር መንግሥት ቱሪዝምን አንዱ የኢኮኖሚ ምሰሶ በማድረግ በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገር እና ገበታ ለትውልድ ተነሳሽነቶች አማካኝነት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ዘመናዊ የቱሪስት መዳረሻዎችን ገንብቷል። እነዚህ ግዙፍ የቱሪዝም መዳረሻ የልማት ሥራዎች የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎችን ቀልብ በመሳብ ኢትዮጵያን ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ በማድረግ ከዘርፉ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ አስችለዋታል። በገበታ ለሸገር ከተገነቡት የቱሪዝም መዳረሻዎች መካከል የአንድነት ፓርክ የመዲናዋን ማራኪነት በማጎልበት በጎብኚዎች ተመራጭ እንድትሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ወዳጅነት ፓርክ አንድ እና ሁለት አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ገጽታዋን ከዘመናዊ ቱሪዝም ጋር አጣጥማ እንድታስቀጥል ምቹ ዕድል ፈጥረዋል። የአንድነት ፓርኮች ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ነጃት ግርማ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ ፓርኮቹ ባለፉት ዓመታት በርካታ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ጎብኚዎችን መሳብ ችለዋል። የፓርኮቹ ተገንብቶ አገልግሎት መስጠት ለበርካታ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም ተናግረዋል። በተጨማሪም ፓርኮቹ የተለያዩ ሁነቶችን በማስተናገድ ከፍተኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እንዲፈጠር ማስቻላቸውን ጠቁመዋል፡፡ ይዘት ፈጣሪዎች ሥራዎቻቸውን የሚያከናውኑበት ተመራጭ ማዕከል መሆን መቻላቸውን ጠቅሰው፤ የተለያዩ የንግድ ተቋማት በፓርኩ ሥራቸውን በተሻለና ምቹ በሆነ መልኩ እንዲያከናወኑ ማድረጉን ተናግረዋል። ይህም የኢኮኖሚ ፍሰቱን በማሳለጥ በኩል አወንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በፓርኩ ሲዝናኑ ያገኘናቸው ወጣቶች በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በቱሪዝም ዘርፍ ያላትን እምቅ አቅም ለመጠቀም እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የሚደነቁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡   ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል ናሆም ተስፋዬ፣ በአሁኑ ወቅት የአንድነት ፓርክን ጨምሮ በተለያዩ አካባቢዎች በርካታ የቱሪዝም መሠረተ ልማቶች መገንባታቸው በርካታ ጠቀሜታ እንዳላቸው ተናግሯል፡፡ ይህም ለሀገር ውስጥና ለውጭ ጎብኚዎች መሳብ እንዲሁም የኢትዮጵያን ገጽታ በመገንባት በኩል አበርክቷቸው ከፍተኛ መሆኑን ጠቁሟል፡፡ በመዲናዋ የተገነቡ እና እየተገነቡ የሚገኙ የቱሪስት መስህብ ስፍራዎች ለከተማዋ የቱሪዝም ዘርፍ መነቃቃት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን የገለጸችው ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ቤዛ ክፍሌ ናት፡፡   በከተማዋ የተገነባው የአንድነት ፓርክም ለጎብኚዎች ምቹ እና ተመራጭ የመዝናኛ ስፍራ ከመሆን ባለፈ ለቱሪዝም እድገት የራሱን ከፍተኛ ሚና እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጻለች፡፡   ሌላው አስተያየት ሰጪ ወጣት ሀንደሰ ዓለሙ በበኩሉ፣ አንድነት ፓርክ ለወጣቶች የስራ ትስስር እና የሀሳብና ልምዶችን የሚጋሩበት ምቹ አውድ መፍጠሩን ገልጿል፡፡  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም