ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በዘላቂ ሰላምና ልማት ስራዎች ሚናችንን እናጠናክራለን-የመንግስት ሰራተኞች
Aug 10, 2026 149
ገንዳውኃ፣ ነሃሴ 4/2018 (ኢዜአ):- ዘላቂ ሰላምን በማስፈን ልማትን አጠናክሮ ለማስቀጠል በሚከናወኑ ተግባራት ሚናቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በምዕራብ ጎንደር ዞን የገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር የመንግስት ሰራተኞች ገለጹ። የከተማው አስተዳደር ከመንግስት ሠራተኞች ጋር በሰላም፣ ጸጥታ እና በልማት ስራዎች ዙሪያ ምክክር አካሂዷል። በውይይት መድረኩ የተሳተፉ የመንግስት ሰራተኞች በከተማው በሚከናወኑ በዘላቂ ሰላምና ልማት ስራዎች ሚናቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። ከሰራተኞች መካከል አቶ በረከት ገብሬ እንደገለጹት፣ ሰላምን በዘላቂነት ማረጋገጥ ለልማት ስራዎች መፋጠን ወሳኝ ነው ። ሰላምን በዘላቂነት በማረጋገጥ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ዳር ለማድረስ በሚከናወኑ ተግባራት ሚናቸውን እንደሚያጠናክሩ አመልክተዋል ። "የመንግስት ሰራተኛው የህብረተሰቡ ግንባር ቀደም አገልጋይ እንደመሆኑ መጠን፣ የአካባቢውን ሰላም በማስጠበቅ እና የጸጥታ ስጋቶችን ቀድሞ በመከላከል ረገድ አርአያነታችንን ማሳየት አለብን" ብለዋል። ከድጃ ሙሳ በበኩላቸው፣ የህዝቡን የአገልግሎት ፍላጎት በታማኝነትና በጥራት ማሟላት ለሰላም መረጋገጥ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመዋል። "በየመሥሪያ ቤታችን ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ለዘላቂ ሰላምና ልማት መረጋገጥ አበርክቷችንን እናጠናክራለን ብለዋል ። የገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ አቶ አዳነ ሀሰን በበኩላቸው፣ በከተማ አስተዳደሩ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን በፍጥነት ለማጠናቀቅ የሰራተኛው ተነሳሽነት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በየደረጃው በመፍታት፣ ሰላምን የሚያጽኑና የአገልግሎት አሰጣጥን የሚያፋጥኑ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። የምዕራብ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ በወቅቱ እንዳሉት፣ የመንግስት ሰራተኛው የመልካም አስተዳደርና የልማት ስራዎችን ግንባር ቀደም መሪ ሆኖ ሊፈፅም ይገባል። በተለይም ሰላምን በዘላቂነት የማረጋገጥ ስራ የሁሉም መሰረት መሆኑን አመልክተዋል ። ሰራተኛው ከህብረተሰቡ ጋር በቅርበት በመስራት የሰላም አምባሳደር ሊሆን እንደሚገባ እና ለአካባቢው ደህንነት መጠበቅ የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል ።
የኦዲት ጥራትን ለማሻሻል ባለሙያዎች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ታሳቢ በማድረግ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል
Aug 10, 2026 212
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፦የኦዲት ጥራትን ለማሻሻል ባለሙያዎች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ታሳቢ በማድረግ በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ ገለጸ። የኢትዮጵያ ሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ በኦዲት ጥራት የግምገማ ውጤቶች ዙሪያ ከኦዲት ባለሙያዎችና ባለድርሻ ተቋማት ጋር ተወያይቷል። የቦርዱ ዋና ዳይሬክተር ውብእሸት ታደለ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኦዲተሮች የሒሳብና የኦዲት ሪፖርቶችን ጥራት ለማረጋገጥ ዓለም አቀፍ የሙያ ደረጃዎችንና የሥነ-ምግባር መርሆዎችን በጥብቅ ክትትል ነጻና ገለልተኛነት ሆነው ሊሰሩ ይገባል። በግምገማው የታዩ የኦዲት ጥራት ክፍተቶችን ለመሙላት የባለሙያዎችን አቅም ማጎልበት፣ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማስፋፋትና የሙያ ደረጃዎችን ማስጠበቅ አስፈላጊ መሆኑም አስገንዝበዋል። የቦርዱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ አጎናፍር በበኩላቸው፤ ጥራት ያለው የኦዲት ሪፖርት ኢንቨስትመንትን ለመሳብ፣ የታክስ ሥርዓቱን በብቃት ለማስኬድና የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማጠናከር ወሳኝ ሚና እንዳለው ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ወደ ካፒታል ገበያ እየተሸጋገረች በመሆኑም ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀ የኦዲት ሥርዓት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ኦዲተሮች ለሒሳብ አያያዝና ኦዲት ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ መልዕክት አስተላልፈዋል። የውጭ ኦዲተሮች ማኅበር ፕሬዝዳንት ዳንኤል ጌታነህ፤ የኦዲት ድርጅቶች የሰው ኃይልና የቴክኖሎጂ አቅማቸውን መፈተሽና ክፍተት ያለባቸውን ማጠናከር የኦዲት ጥራትን ለማሻሻል ቁልፍ ነው ብለዋል። የኮከብና መልካሙ ኦዲት አድራጊ ድርጅት ተወካይ ኮከብ ሞገስ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የአካውንቲንግ ትምህርት ከንድፈ ሀሳብ ባሻገር የተግባር ልምምድን ያካተተ እንዲሆን በማድረግ ብቁ የሒሳብና የኦዲት ባለሙያዎችን ማፍራት እንደሚገባ ጠቁመዋል። ውይይቱም በኦዲት ጥራት የታዩ ክፍተቶችን በመለየት የጋራ መፍትሔ ለማስቀመጥ ያለመ መሆኑ ተገልጿል።
በክልሉ በንግድና በገቢ ተቋማት የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በማረም ውጤታማ ሥራ ለማከናወን የተጀመረው ቅንጅታዊ ሥራ ይጠናከራል-ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Aug 10, 2026 151
ሆሳዕና፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በንግድና በገቢ ተቋማት የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በማረም ውጤታማ ሥራ ለማከናወን በቅንጅት የሚሰራው ሥራ እንደሚጠናከር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። በክልሉ ገቢዎች እና ንግድና ገበያ ልማት ቢሮዎች በህገ ወጥ የንግድ ቁጥጥር፣ ገበያ ማረጋጋትና የታክስ ተገዥነትን ማረጋገጥ አስመልክቶ የተዘጋጀ የንቅናቄ መድረክ በሆሳዕና ከተማ ተካሂዷል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንደሻው ጣሰው (ዶ/ር) በመድረኩ ማጠቃለያ እንዳሉት በክልሉ በንግድ እና በገቢ ተቋማት ላይ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በማረም ውጤታማ ተግባራትን ለማከናወን በቅንጅት የሚሰሩ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። በተለይ በንግድ ሥርዓቱ የሚስተዋል ህገወጥነትን ለመከላከል በዘርፉ የወጡ ደንብና መመሪያዎችን ከሚያስፈጽሙ ባለድርሻ አካላት ጋር በቅርበት የሚሰራው ሥራ እንደሚጠናከር ገልጸዋል። በዚህም ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ በማድረግ የኑሮ ውድነቱን ለማባባስ የሚከናወኑ ህገወጥ ተግባራትን በመቆጣጠር ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚሰራው ሥራ ይጠናከራል ብለዋል። በተጨማሪም ክልሉ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን ለማስቀጠልና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ተግባራት እንደሚጠናከሩ ነው እንዳሻው (ዶ/ር) የገለጹት። ለዚህም ገቢን በአግባቡ የመሰበሰብ ሂደቱን የሚያስተጓጉሉ ከተጨማሪ እሴት ታክስና ከደረሰኝ ገቢ አሰባሰብ ጋር የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ለማረም ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ሥራ ይሰራል ብለዋል። በዚህ ረገድ አመራሩ በህብረተሰቡ ተሳትፎ ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል የህዝብን ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ሊተጋ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ሀላፊ ባዩሽ ተስፋዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት፤ በክልሉ በንግድ ምዝገባ፣ ፈቃድ አሰጣጥና እድሳት ላይ በተለያየ መንገድ የሚከሰቱ ችግሮችን ለመፍታት አገልግሎቱን የማዘመን ሥራ እየተሰራ ነው። በገበያ የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት አምራቹንና ሸማቹን የሚያገናኙ ከ100 በላይ ገበያዎችና ሌሎች መደበኛ የግብይት ማዕከላት ለማህበረሰቡ አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በክልሉ በንግድ ሥርዓቱ ላይ የሚስተዋሉ ህገ ወጥ አሰራሮችን በማረም ረገድ የተጀመሩ ተግባራትን ለማጠናከርም ቅንጅታዊ ሥራው እንደሚጠናከር ተናግረዋል፡፡ በክልሉ በበጀት ዓመቱ ከ35 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ ከማህበረሰብ የሚነሱ የልማት ጥያቄዎችን ለመፍታት ግብ ተጥሎ ወደ ተግባር መገባቱን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ሀላፊ ቀመሪያ ረሻድ ናቸው፡፡ ገቢን በአግባቡ የመስበሰብ ሂደቱን የሚያስተጓጉሉ ከተጨማሪ እሴት ታክስና ከደረሰኝ ገቢ አሰባሰብ ጋር የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ለማረም ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ሥራ ይጠናራል ብለዋል፡፡ የክልሉ ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነርና የወንጀልና ትራፊክ አደጋ መከላከል ዘርፍ ሀላፊ ኮሚሽነር አብርሃም ቲርካሶ በበኩላቸው በክልሉ ህገወጥ የንግድ እንቅስቃሴና የኮንትሮባንድ ዝውውርን ለመከላከል እየተሰራ ነው። በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮች እንዲታረሙ ከሚሽኑ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ህግ የማስከበር ሥራውን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያሳደገልን ነው
Aug 10, 2026 183
ጊምቢ፣ ነሐሴ4/2018 (ኢዜአ) ፡-በምዕራብ ወለጋ ዞን እየተተገበረ የሚገኘው የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንዳስገኘላቸው ነዋሪዎች ገለጹ። የ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃ-ግብር በኢትዮጵያ በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ ያለ ሀገራዊ የልማት ንቅናቄ ሲሆን፤ ዋና ዓላማውም በግብርናው ዘርፍ በዶሮ፣ በወተት፣ በማር፣ በበግና ፍየል ማድለብ እንዲሁም በዓሳ እርባታ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ነው። መርሃ-ግብሩ በቤተሰብ ደረጃ የምግብና የሥርዓተ-ምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ የሀገር ውስጥ ምርትን በማሳደግ፣ የገበያ አቅርቦትን በማሻሻል እና ለዜጎች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ በመፍጠር ረገድም ትልቅ ድርሻ አለው። በዚሁ መሠረት በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን የመርሃ-ግብሩን አፈጻጸም ውጤታማ ለማድረግ ሰፊ እንቅስቃሴ ሲደረግ ቆይቷል። በዞኑ የሚገኙ አርሶ አደሮችና የአካባቢው ነዋሪዎች በዘመናዊ መንገድ የዶሮ እርባታ፣ የወተት ላሞች እንክብካቤ እና የማር ንብ እርባታ ላይ በስፋት እንዲሰማሩ መደረጉ ተገልጿል። ይህ እንቅስቃሴም በየቤተሰቡ ደረጃ ንጹህ እና የተመጣጠነ ምግብ በቀላሉ እንዲገኝ አስችሏል፤ አርሶ አደሮችና ወጣቶች ከዘርፉ የሚያገኙትን ትርፍ ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንዲፈጥሩና የኑሮ ደረጃቸውን እንዲያሻሽሉም አድርጓል። በዞኑ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በመሳተፍ ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል የኢናንጎ ከተማ ነዋሪ አቶ ሂካ ኩመራ እና አለምነሽ አብዲ እንዳሉት አምስት የወተት ላሞች በማርባት በቀን በአማካይ 150 ሊትር ወተት እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በከተማ አስተዳደሩ በተፈጠረላቸው ድጋፍና ዕድል በወተት ላም እርባታ ዘርፍ መሰማራታቸው፣ የኑሮ ደረጃቸውን ለማሻሻልና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። ወይዘሮ ዲርቤ ሌሊሳ በበኩላቸው 300 እንቁላል ጣይ ዶሮዎችን በማርባት በሥራቸው ትርፋማ መሆን መቻላቸውን ገልጸዋል። በዚህም ለአካባቢው ማህበረሰብ እንቁላል በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ማድረጋቸውንና የራሳቸውን ገቢ ማሳደጋቸውን ገልጸው፤ በተጨማሪም ለልጆቻቸው የተመጣጠነ ምግብ ለማቅረብ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። ወጣት ሙቤ ቃሲም በበኩሉ ከቤተሰቦቹ ጋር በመሆን በ500 ዶሮዎች የጀመረው የእርባታ ሥራ አሁን ላይ ውጤታማ እያደረገው መሆኑን ገልጸዋል። የእንቁላል እና የሥጋ ዶሮዎችን ለገበያ በማቅረብ በሥራው ትርፋማ እየሆነ መምጣቱንም ተናግሯል። የምዕራብ ወለጋ ዞን የኢናንጎ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዳንኤል በዳሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተማዋ የሕዝቡን የልማት ጥያቄዎች የመመለስ ሥራዎችን ከመስራት ጎን ለጎን የህብረተሰቡን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በተለይም በ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃ-ግብር ዝርያቸው የተሻሻሉ የወተት ላሞች፣ ዶሮዎች እና የንብ ቀፎዎች ለአካባቢው ነዋሪዎች እየቀረቡ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የምዕራብ ወለጋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት የእንስሳት ልማት እና ዝርያ ማሻሻያ ቡድን መሪ አቶ ገመቺስ ታደሰ፤ በ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃ-ግብር በርካታ ወገኖችን ተጠቃሚ ማድረግ ያስቻሉ ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል። በተለይም ዝርያቸው የተሻሻሉ የወተት ላሞች አቅርቦትና በዶሮ እርባታ ልማት ላይ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃግብር 5 ነጥብ 7 ሚሊዮን የዶሮ ጫጩቶች ለአርሶ አደሮችና ወጣቶች የተሰራጩ ሲሆን፤ 5 ሺህ ላሞችን በማዳቀልም 90 ሚሊዮን 58 ሺህ ሊትር የወተት ምርት ማግኘት ተችሏል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪም በዞኑ በ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃ-ግብር አማካኝነት የዓሳ እርባታ መንደሮች በስፋት እየተገነቡ እንደሚገኙ አስረድተዋል።
በአማራ ክልል ከዘንድሮ ዓመት የበልግ ሰብል ልማት ከሶስት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተሰበሰበ
Aug 10, 2026 252
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በበልግ ወቅት ከለማው ሰብል ከሶስት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የሰብል ልማት ባለሙያ ወይዘሮ እንዬ አሰፋ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በመኸር፣ በመስኖና በበልግ ልማት የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት እየተቻለ ነው። በበጋው ወቅትም የበልግ አብቃይ በሆኑ ዞኖች 247 ሺህ 367 ሄክታር መሬት በማልማት ከሶስት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል። የተገኘው ምርትም የገብስ፣ ስንዴ፣ አኩሪ አተር፣ ቦሎቄ፣ ጤፍ፣ ማሾና ሌሎች ሰብሎች መሆኑን ጠቁመው፤ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የሁለት ሚሊዮን ኩንታል ብልጫ አለው ብለዋል። ይህም አርሶ አደሩ የምግብ ዋስትናውን እያረጋገጠ እንዲመጣ ከማድረግ ባለፈ፤ ለኢንዱስትሪ ግብአትና ለወጭ ንግድ የሚሆን ምርት በማምረት ተጠቃሚ እንዲሆን እያስቻለ መሆኑን ተናግረዋል። በደቡብ ወሎ ዞን የተሁለደሬ ወረዳ አርሶ አደር ኢብራሂም አህመድ በሰጡት አስተያየት፤ በዘንድሮው የበልግ ዝናብ አንድ ሄክታር ተኩል ማሳቸውን ቦሎቄና ሽምብራ በመዝራት የተሻለ ምርት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ይህም በምግብ ራሴን እንድችል ከማድረግ ባለፈ ከምግብ ፍጆታ የተረፈውን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እንድሆን አስችሎኛል ብለዋል። የበልግ ዝናብ ስርጭቱ የተሻለ በመሆኑ በግማሽ ሄክታር መሬት ካለሙት የገብስ ሰብል 15 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ በሰሜን ሸዋ ዞን የጣርማ በር ወረዳ አርሶ አደር አሰፋ መኮነን ናቸው። በ2017 በጀት ዓመት በክልሉ በበልግ ሰብል ከለማው ከ146 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ከአንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በአዳማ ከተማ ከ25 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን መሬት ታርሶ በዘር ተሸፍኗል
Aug 10, 2026 210
አዳማ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፡-በአዳማ ከተማ ከልማት ሥራዎች ጎን ለጎን ከ25 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን መሬት ታርሶ በዘር መሸፈኑን የከተማዋ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። አዳማ ከኦሮሚያ ክልል ዋነኛ የኢኮኖሚ፣ የኢንዱስትሪ እና የትራንስፖርት ማዕከላት መካከል አንዷ በመሆኗ ፈጣን የከተማ ማስፋፋትና የህዝብ ቁጥር እድገት የሚታይባት ከተማ ናት። የከተማዋ የቆዳ ስፋትና የመሰረተ ልማት ዝርጋታ በየጊዜው እያደገ ቢመጣም፣ ከተማን ከአካባቢ ጥበቃ እና ከምግብ ዋስትና ጋር አጣጥሞ ማስኬድ አስፈላጊ ነው። ይህ እርምጃ የከተሞች ህዝብ ቁጥር መጨመርን ተከትሎ የሚከሰተውን የምግብ ፍላጎት ለማሟላት እና አትክልትና ሰብል ምርቶች አቅርቦትን ጨምሮ የዋጋ ንረትን ለመቀነስ፣ እንዲሁም ለወጣቶች እና ለሴቶች በከተማ ግብርና እና በዘመናዊ የእርሻ ስራዎች የስራ እድል ለመፍጠር ታስቦ የሚተገበር ይሆናል። የአዳማ ከተማ ግብርና ጽሕፈት ቤት እንደገለፀው ከ25 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑ፣ ከተማዋ የማኑፋክቸሪንግ እና የንግድ ማዕከልነቷን እንደጠበቀች የግብርና ምርታማነቷንም ጎን ለጎን ለማሳደግ እያደረገች ያለውን ጥረት የሚያሳይ ነው። የጽሕፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ አለሙ ቂልጡ ለኢዜአ እንደገለጹት በ2018/19 የምርት ዘመን የከተማዋን አርሶ አደር ምርትና ምርታማነት ለመጨመር በተሻለ ደረጃ የምርት ማሳደጊያ ግብዓት ቀርቧል። ከምስራቅ ሸዋ ዞን አዳማ ወረዳና ሉሜ ወረዳ 28 የገጠር ቀበሌዎችን በማጠቃለል እንደገና የተደራጀችው አዳማ፤ በሺህዎች የሚቆጠሩ አርሶ አደሮች ወደ ከተማዋ መቀላቀላቸውንም ሃላፊው ገልጸዋል። በዚህም ከተማዋ የነበራት የእርሻ መሬት ከእጥፍ በላይ ማደጉን የገለጹት አቶ አለሙ፤ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የእርሻ አሰራር ስርዓቱ በቴክኖሎጂና በሜካናይዜሽን የታገዘ እንዲሆን በተደረገው ጥረት ውጤት እየተመዘገበ ነው ብለዋል። ለዘንድሮ የመኽር እርሻ ልማት በአስተዳደሩ 20 የእርሻ ትራክተሮች ተገዝተው ለአርሶ አደሩ መሰጠቱን ገልጸው፤ እስካሁን 25ሺህ 154 ሄክታር መሬት በስንዴ፣ ጤፍ፣ ቦቆሎና ጥራጥሬን ጨምሮ በዋና ዋና ሰብሎች ተሸፍኗል ብለዋል። በመኽር እርሻው ከ50ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘርና ፀረ አረም መድሃኒቶች ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱንም አቶ አለሙ ጨምረው ገልጸዋል። በተጨማሪም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የከተማዋን አርሶ አደር ህይወት ከመሰረቱ ለመለወጥ ከዋና ዋና የሰብል ልማት ባለፈ ተጨማሪ ገቢ ማስገኘት የሚችሉና ከውጭ የሚገቡ የግብርና ምርቶችን መተካት በሚችሉት የፍራፍሬ ልማት ላይ በትኩረት እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። በዚህም በከተማ አስተዳደሩ ከ100 ሄክታር በላይ መሬት ላይ አቮካዶ፣ ብርትኳን፣ ሎሚ፣ ፓፓየ፣ ዘይቱንና ማንጎ በስፋት እየለማ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በተለይም የአዋሽ ወንዝን ጨምሮ የመስኖ ውሃ ተቋማትን በመጠገንና የውሃ መሳቢያ ሞተሮችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ በዓመት ከሶስት ጊዜ በላይ የማምረት ሂደት ባህል እንዲሆን እንደሚሰራም ተናግረዋል።
የአፋር ክልል ምክር ቤት ለ2019 በጀት ዓመት ከ33 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ አፀደቀ
Aug 10, 2026 252
ሰመራ ፤ ነሐሴ 4/2018(ኢዜአ) ፦ የአፋር ክልል ምክር ቤት ለ2019 በጀት ዓመት ከ33 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ በጀት አፀደቀ። ምክር ቤቱ ነሐሴ 2ቀን 2019 ዓ.ም የጀመረው 6ኛ የምርጫ ዘመን፣ 5ኛ የሥራ ዘመን፣ 10ኛ መደበኛ ጉባዔውን በሰመራ ከተማ ማካሄዱን ቀጥሏል። በጉባዔው ተገኝተው የክልሉን የ2019 ረቂቅ በጀት ያቀረቡት የገንዘብ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ደረሳ መሐመድ እንዳሉት፤ በጀቱ ከመንግሥት ድጎማ ከክልሉ የውስጥ ገቢ፣ ከፌዴራልና ከተለያዩ ሌሎች አማራጮች የሚሸፈን ነው። ለበጀት ዓመቱ የተመደበው ገንዘብ የክልሉን ልማት ለማቀላጠፍና የሕዝቡን ጥያቄዎች ለመመለስ የሚያስችል ከመሆኑም በላይ የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚረዳ መሆኑንም አመላክተዋል። ምክር ቤቱ ከበጀቱ በተጨማሪ ሁለት የተለያዩ ረቂቅ አዋጆችን ያፀደቀ ሲሆን፤ ቀጥሎም የዳኞችን ሹመት ያፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል።
ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ የህዝብን የልማት ጥያቄ የመመለስ ተግባራት ይጠናከራሉ - ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Aug 10, 2026 241
ሆሳዕና፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ የህዝብን የልማት ጥያቄ የመመለስ ተግባራት እንደሚጠናከሩ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። የክልሉ ገቢዎች እና ንግድና ገበያ ልማት ቢሮዎች በሕገ-ወጥ የንግድ ቁጥጥር፣ ኑሮን በማረጋጋትና የታክስ ሕግ ተገዢነትን በማረጋገጥ ዙሪያ የተዘጋጀ የንቅናቄ መድረክ በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ይገኛል። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ የሕዝቡን የልማት ጥያቄዎች የመመለስ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ የገቢ አቅምን በማሳደግ የከተሞችን ገጽታ የመቀየር፣ የመሠረተ ልማት ተደራሽነትን የማስፋትና የማህበረሰቡን ሕይወት ለማሻሻል በተከናወኑ ተግባራት የተመዘገቡ ስኬቶች ይጠናከራሉ ብለዋል። በሌላ በኩል በክልሉ የንግድ ሥርዓቱን በማዘመን የተሳለጠ አሠራር መዘርጋት አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል። ለዚህም ሕገ-ወጥነትን የመከላከል፣ የግብይት ማዕከላትን የማስፋፋት፣ ምርትን በበቂ ሁኔታ የማቅረብ፣ የዋጋ ንረትን የመቆጣጠርና የሸማች ማኅበራትን የማጠናከር ሥራዎች እንደሚከናወኑ አክለዋል፡፡ በዘርፉ የሚከናወኑ ተግባራት ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን ለማሳለጥና የኑሮ ውድነቱን ለማረጋጋት ወሳኝ በመሆናቸው፣ መስተዳድሩ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅታዊ ሥራ ማጠናከር የትኩረት አቅጣጫው ማድረጉንም ገልጸዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር የመንግሥትና የፓርቲ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
ኦዲተሮች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን በመተግበር ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል
Aug 10, 2026 241
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ) ፦ ኦዲተሮች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን በመተግበር ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድ አመለከተ። ቦርዱ በኦዲት ጥራት የግምገማ ውጤቶች ዙሪያ ከኦዲተሮች ጋር እየተወያየ ይገኛል። የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ አጎናፍር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኦዲተሮች ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል። የሂሳብ ሪፖርቶችን ጥራት የሚያስጠብቁ ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ጠብቆ መስራት ላይ ውስንነቶች መኖራቸውን የግምገማ ውጤቱ እንደሚያመላክት ጠቁመው ኦዲተሮች ይህንን ክፍተት ለመሙላት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ነጻ እና ገለልተኛ ሆኖ በሃላፊነት መስራት ከኦዲተሮች የሚጠበቅ ሌላው ሙያዊ ግዴታ መሆኑን ጠቁመው የስነ ምግባር መርሆዎችን ጠብቆ መስራት እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። ጥራቱን የጠበቀ የሂሳብ ሪፖርት ኢንቨስትመንት ለመሳብ፣ ለታክስ ስርአት ውጤታማነት እንዲሁም ለሀገር ኢኮኖሚ መሳለጥ ትልቅ ሚና እንዳለውና ለስኬታማነቱ የኦዲተሮች ሙያዊ ደረጃዎችን ጠብቆ መስራት ቁልፍ ድርሻ አለው ብለዋል። እንደ ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ ገለጻ፤ ኢትዮጵያ ወደ ካፒታል ገበያ ስርአት እየገባች በመሆኑ ጥራትና ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የኦዲት ስርአት አስፈላጊ ነው። የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድም የኦዲተሮችን አቅም በመገንባት ለዘርፉ ውጤታማነት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የውይይት መድረኩ በኦዲት ጥራት ክፍተቶች ዙሪያ በመመካከር የጋራ መፍትሔ ለማመላከት መሆኑን ጠቁመዋል።
በደቡብ ወሎ ዞን እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ በመቀየር ለእንቅስቃሴና ለልማት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Aug 10, 2026 398
ደሴ ፤ ነሐሴ 4/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ በመቀየር እንዲነቃቁ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የዞኑ ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የመሰረተ ልማት ቡድን የኮንስትራክሽን አስተዳደር መሃንዲስ አደም መሃመድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በሐይቅ፣ ጊምባ፣ መካነሰላም፣ ሀርቡ፣ ወረኢሉ፣ አቀስታ እና ደጎሎ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ እየተካሔደ ነው። በነዚሁ አካባቢዎች በመገንባት ላይ ካለው 6 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ ውስጥም ከሁለት ኪሎ ሜትር በላይ የሚሆነው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑን ተናግረዋል። የኮሪደር ልማቱ ከተሞችን በማስዋብና ገጽታቸውን በመቀየር እንዲነቃቁ ከማድረጉ ባለፈ ለነዋሪዎች፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል። ቀሪውን ሥራ በፍጥነትና በጥራት አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት ሰፊ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም አክለዋል። ልማቱ የእግረኛና የብስክሌት መንገዶችን፣ መዝናኛዎችንና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን ያካተተ በመሆኑ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረጉን ነው የጠቀሱት። ማሕበረሰቡ ለግንባታ ስራው በገንዘብ፣ በጉልበትና ቁሳቁስ በማቅረብ ከፍተኛ ተሳትፎ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። የሐይቅ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ እናትነሽ በሽር በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማቱ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉ ከተማዋን ከማነቃቃቱ በላይ ለነዋሪዎች ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል። በተለይም የእግረኛ፣ የተሽከርካሪና የብስክሌት መንገዶችን እንዲሁም መዝናኛዎችን ማካተቱ የትራፊክ አደጋን በማስቀረት በነጻነት ለመንቀሳቀስ አስችሎናል ነው የሚሉት። ሌላው የዚሁ ከተማ ነዋሪ ሸህ ጀማል ለይሱ፤ ልማቱ የከተማዋን ገጽታ በማሳመርና በማስዋብ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ነው ያብራሩት። ህብረተሰቡ በገንዘብ፣ በቁሳቁስና በጉልበት ያደረገው አስተዋጽኦ የግንባታ ስራው በፍጥነትና በጥራት ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ ማድረጉን ገልፀዋል።
በጋምቤላ ክልል በተያዘው የመኸር ወቅት ከ86 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰሊጥ ለምቷል
Aug 10, 2026 256
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በተያዘው የመኸር ወቅት ከ86 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሰሊጥ ልማት መከናወኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ አስታወቀ። የጋምቤላ ክልል ሰፊና ለም መሬት፣ በቂ የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር የውሃ ሀብት እንዲሁም ለተለያዩ የግብርና ምርቶች ተስማሚ የሆነ አየር ንብረት ያለው አካባቢ ነው። ክልሉ በተለይም ለቅባት ሰብሎች አመቺ በመሆኑ በሀገሪቱ የግብርና ኢንቨስትመንት ከተመረጡ ዋና ዋና አካባቢዎች አንዱ ያደርገዋል። ባለፉት ዓመታት በክልሉ የሚካሄደው የቅባት ሰብሎች ልማት በዋናነት በባህላዊ መንገድ በአርሶ አደሮችና በጥቂት ባለሃብቶች የተወሰነ የነበረ፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በዘመናዊ የግብርና ግብአቶች እና በሜካናይዜሽን ታግዞ በፍጥነት እያደገ ይገኛል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ኡጀሉ ኡሞድ ለኢዜአ እንደገለጹት ክልሉ የቅባት ሰብሎችን ጨምሮ ለሁሉም የግብርና ልማት ምቹ ስነ- ምህዳር ያለው አካባቢ ነው። ክልሉ ለሁሉም የግብርና ልማት የተመቸ ከመሆኑ ጋር ተያይዞም የቅባት እህሎችን ጨምሮ በሌሎች ሰፋፊ የግብርና ልማት ለመሰማራት በርካታ ባለሃብቶች ወደ ክልሉ እየገቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በክልሉ በዘንድሮው የመኸር እርሻ በባለሃበቶችና በአርሶ አደሮች ከ86 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰሊጥ መልማቱን ገልጸዋል። በክልሉ በዘንድሮው የመኸር ወቅት የለማው መሬት ከቀዳሚው ዓመት ጋር ሲነፃፀር ከ20 ሺህ ሄክታር በላይ ብልጫ ያለው መሆኑን አስረድተዋል። በክልሉ ከለማው ሰሊጥም ከ516 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ሊሰበሰብ እንደሚችል ጠቁመው፤ አሁን ላይ ያለው የሰብሉ ቁመና የተሻለ ስለሆነ ከተጠበቀው በላይ ምርት ሊገኝ ይችላል የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል። በክልሉ አቦቦ ወረዳ በሰሊጥ ሰብል ልማት ከተሰማሩት ባለሃብቶች መካከል አቶ እየሩስ ዓለሙ በሰጡት አስተያየት የዘንድሮው ክረምት የዝናብ ስርጭት ቀለል ያለ በመሆኑ ለሰሊጥ ሰብል ምቹ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በ120 ሄክታር መሬት ላይ ያለሙት ሰብል ደርሶ በመሰብሰብ ሂደት ላይ መሆኑን ጠቁመው የዘንድሮው የሰሊጥ ምርት በብዛትም ሆነ በጥራት የተሻለ መሆኑን ተናግረዋል።
የአፍሪካ የውሃ ማማ ኢትዮጵያ ሳትሆን ግብፅ ናት!
Aug 10, 2026 281
ግብጽ ራሷን የምትስልበት የውሃ እጥረት ትረካ ከነባራዊ ሁኔታም በእጅጉ የተቃረነ ነው። የአፍሪካን የታሪክ፣ የኢኮኖሚና ጂኦ-ፖለቲካ በከፍተኛ ሁኔታ ከሚቃኙት ተፈጥሯዊ ሃብቶች መካከል ውሃ ግንባር ቀደሙን ስፍራ ይይዛል። አፍሪካውያን የውሃ ሀብታቸውን በጋራ አልምቶ የመጠቀም ፍላጎታቸውና ጥረታቸው የአህጉሪቱን የወደፊት የልማትና የሰላም አቅጣጫ የሚወስን ወሳኝ ጉዳይ ቢሆንም ይህ አህጉራዊ የትብብርና የጋራ እድገት መንፈስ እውን ሊሆን የሚችለው የተፋሰሱ ሀገራት ያላቸውን እውነተኛ የውሃ ሀብት መጠንና ፍላጎት በሳይንሳዊ እውነታዎችና በግልጽኝነት ላይ ተመስረተው ሲተገብሩት ብቻ ነው። በዚህ አህጉራዊ የተፋሰስ ትብብር ውስጥ ትልቁን ስፍራ የሚይዘው የታላቁ ዓባይ ወንዝ ተፋሰስ ነው። ሆኖም ለዘመናት የዘለቀውና አሁንም ድረስ በዲፕሎማሲው መድረክ የሚንጸባረቀው ዋነኛው ማነቆ ግብፅ እራሷን "ለከፍተኛ የውሃ እጥረት የተጋለጠችና ፍጹም የዓባይ ጥገኛ የሆነች ብቸኛ ሀገር" አድርጋ የምታቀርብበት ትርክት ነው። ይህ ትረካ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብን ሲያደናግር ቆይቷል። ነገር ግን የጂኦግራፊ፣ የሃይድሮሎጂና የዘመናዊ ቴክኖሎጂ መረጃዎችን በጥልቀት ስንመረምር ግብፅ እራሷን የምትስልበት የውሃ እጥረት ትረካ ከእውነተኛው ነባራዊ ሁኔታ ጋር በእጅጉ የሚቃረን ሆኖ እንገኘዋለን። ግብፅ በውስጧ የያዘቻቸውን ግዙፍና ያልተነኩ ድብቅ ሀብቶች፣ የቴክኖሎጂ አቅሞችን እና በበረሃ ውስጥ የምታከናውናቸውን ሰፋፊ የውሃ ማዞር ፕሮጀክቶች ስንመለከት ሀገሪቱ እውነተኛ የውሃ እጥረት ሳይሆን ከፍተኛ የውሃ ሀብት ያላት መሆኗን በግልጽ ያሳያል። ይህንን እውነታ በግልጽ የሚያስረዱትንና የግብፅን እውነተኛ የውሃ ማማነት የሚያረጋግጡትን ዋና ዋና ሳይንሳዊና ተግባራዊ ማስረጃዎች እንደሚከተለው ቀርበዋል፦ የከርሰ ምድር ውሃ ከገፀ-ምድር ውሃ ባሻገር በግብፅ፣ ሊቢያ፣ ሱዳን እና ቻድ ስር የሚገኘው የኑቢያ አሸዋማ ድንጋይ የከርሰ-ምድር ውሃ ስርዓት (Nubian Sandstone Aquifer System) በዓለም ላይ ካሉ የከርሰ-ምድር ውሃዎች ትልቁ ነው። አንዳንድ ጥናቶች እንደሚያመላክቱት በግብፅ ግዛት ስር ብቻ የሚገኘው የዚህ ውሃ መጠን ከ5 ትሪሊዮን እስከ 10 ትሪሊዮን ኪዩቢክ ሜትር እንደሆነ ይገመታል። ይህ ግዙፍ ሀብት የዓባይ ወንዝን የአምስት ክፍለ-ዘመናት (500 ዓመታት) አጠቃላይ የውሃ ፍሰት የሚበልጥ ድብቅ ሃብት ነው። ግብፅ ይህንን ሀብቷን በዘመናዊ መንገድ አውጥታ ብትጠቀም ለበርካታ አስርት ዓመታት ያለ ምንም የገፀ-ምድር ውሃ ስጋት መኖር የሚያስችላት ስትራቴጂካዊ ክማቸት አላት ማለት ነው። የአስዋን ከፍተኛ ግድብና የናስር ኃይቅ የግብፅ የውሃ መከላከያ ማዕከል የሆነውና በአስዋን ከፍተኛ ግድብ የተገደበው ናስር ሀይቅ እስከ 169 ቢሊዮን ኩቢክ ሜትር ውሃ የመያዝ አቅም አለው። ይህም ማለት በናስር ሃይቅ የተከማቸው ውሃ ብቻ የግብፅን የዓመታት ሙሉ የውሃ ፍላጎት ያለ ምንም ተጨማሪ የወንዝ ፍሰት መሸፈን የሚያስችል ግዙፍ ስትራቴጂካዊ መያዣ (Buffer) ሆኖ ያገለግላል። የባሕር ውሃ ማጣራት አቅምና የግብጽ 2050 ማስተር ፕላን ግብፅ በሜዲትራኒያን እና በቀይ ባህር ረጅም የባህር ዳርቻዎች ያሏት በመሆኑ በጨዋማ ውሃ ማጣሪያ ቴክኖሎጂ ትልቅ እርምጃ እየወሰደች ትገኛለች። በአሁኑ ወቅት በቀን ከ1 ነጥብ 5 እስከ 2 ሚሊዮን ኪዩቢክ ሜትር የተጣራ ውሃ እያመረተች ሲሆን፤ በግልና በሕዝብ ፣ በካርቦን ቅነሳ ድጋፎች እና በባህር ዳርቻ ማስፋፊያ ፕሮጀክቶች አማካኝነት የማጣራት አቅሟን በጥሬው በእጥፍ ለማሳደግ የሚያስችል እስከ 2050 የሚዘልቅ ስትራቴጂካዊ ማስተርፕላን አዘጋጅታለች። ግዙፍ የውሃ ማዞር ፕሮጀክቶች ግብጽ በቶሽካ ፕሮጀክት አማካኝነት ከናስር ሀይቅ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ኩቢክ ሜትር ውሃዎችን ወደ ምዕራብ በረሃ በመቀየር ሰው ሰራሽ ሀይቆች እና ክፍት የመስኖ ቦዮች እንዲፈጠሩ አድርጋለች ። በሌላ በኩል በኒው ዴልታ እና ጂሪያን በሚሊዮን ሄክታር መሬት ለማልማት እና አዳዲስ ከተሞችን ለመገንባት የተፈጥሮ የአባይ ወንዝን አቅጣጫ በመቀየር ቢሊዮን ኩቢክ ሜትር ውሃ በመመደብ ላይ ትገኛለች።እነዚህ ፕሮጀክቶች ግብፅ ለትልልቅ የበረሃ ልማቶች የሚተርፍ ትርፍ ውሃ እንዳላት በተግባር የሚያሳዩ ናቸው። ውሃን መልሶ የመጠቀም አቅም ግብፅ ውሃን መልሶ በማጣራት ጥቅም ላይ ለማዋል ትልልቅ የውሃ ማጣሪያ ጣቢያዎችን ለምሳሌ በህር ኤል ባቃር (Bahr El-Baqar plant) ገንብታለች። ሀገሪቱ በየዓመቱ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ኩቢክ ሜትር ፍሳሽ ውሃዎችን መልሳ በመጠቀም ለግብርና በማዋል የምትጠቀመውን እያንዳንዱን የውሃ ጠብታ የማባዛት ከፍተኛ ቴክኖሎጂያዊ አቅም እንዳላት አስመስክራለች። መደምደሚያ አፍሪካውያን የውሃ ሀብታቸውን በጋራ አልምተው ለመጠቀም የሚያደርጉት ጉዞ እውን ሊሆን የሚችለው ግብጽ የምታራምደውን አይነት የተሳሳቱ ትርክቶችን በሳይንሳዊ እውነታዎች መተካት ሲቻል ብቻ ነው። ዓለም አቀፉ ማህበረሰብም ይህን በሚገባ ሊገነዘብ ይገባል። ግብፅ ግዙፍ የከርሰ-ምድር ውሃ፣ ዘመናዊ የውሃ ማጣሪያ ጣቢያዎች፣ ከፍተኛ የውሃ መልሶ መጠቀም አቅም እና በበረሃ ውስጥ ውሃ እስከ ማዞር የሚያስችል ሀብት ያላት ሀገር ናት። ይህም ግብፅ የውሃ እጥረት ያለባት ሀገር ሳትሆን፣ የአፍሪካ የውሃ ማማ መሆኗን በተግባር የሚያሳይ ነው።
በህዳሴው ግድብ ያሰፈርነውን አሻራ በሀገራዊ ምክክሩ በመድገም ጠንካራ ሀገር ለመገንባት የበኩላችንን ሚና እንወጣለን
Aug 9, 2026 559
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 3/2018(ኢዜአ) ፦በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ያሳዩትን የታሪክ አሻራ በሀገራዊ የምክክር ሂደቱ በመድገም ጠንካራ ሀገር በመገንባት ለትውልድ ለማስተላለፍ የበኩላችንን ሚና እንወጣለን ሲሉ ተመካካሪ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር በመሳተፍ ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በመጎብኘት የተሰማቸውን ደስታና ኩራት መግለጻቸውን ፐልስ ኦፍ አፍሪካ ከስፍራው ዘግቧል፡፡ ከሰሜን አሜሪካ ቨርጂኒያ የመጡት ተመካካሪ አድጎልኝ መኮንን በሰጡት አስተያየት እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል ኢትዮጵያ ውስጥ የመንግሥት ሠራተኛ በነበሩበት ወቅት የ400 ብር ቦንድ ገዝተው አስተዋጽኦ ያደረጉበት ግድብ ተጠናቆ በማየታቸው ጥልቅ የደስታ ስሜት ተሰምቷቸዋል። "ዓባይ ግንድ ይዞ ይዞራል" መባሉ ቀርቶ ዛሬ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ትልቅ የብርሃን ምንጭ መሆን መቻሉ ታላቅ ኩራት ነው ብለዋል። አሁን ደግሞ ከመላ ኢትዮጵያና ከውጭ ሀገር የተውጣጡ አራት ሺህ ዜጎች በመካከር ላይ መሆናቸውን አውስተው፤ በምክክር ጉባኤው ላይ ስለሀገራቸው ጉዳይ በነጻነት የሚመካከሩበትን ትልቅ ታሪካዊ ዕድል ለመጀመሪያ ጊዜ አግኝተናል ብለዋል። ዜጎች በመመካከር ጠንካራ ሀገር ለትውልድ ለማስተላለፍ የሚደረገው የሰለጠነ የምክክር ሂደት የሚያስደስት ሆኖ እንዳገኙትም ጠቅሰዋል፡፡ ከሰዊድን የመጡት ተመካካሪ መቅደስ ወርቁ በበኩላቸው፤ በግድቡ ግንባታ ወቅት በውጭ ሀገር ሲያስተባብሩ መቆየታቸውን ገልጸው፤ አሁን ግድቡ ተጠናቆ በአካል ማየት በመቻላቸው ደስታና ኩራት እንደተሰማቸው ተናግረዋል። በግድቡ የተሰራው ድንቅ ተግባር የኢትዮጵያውያንን ገድል እና ዳግማዊ ዓድዋ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ አሁን በመካሄድ ላይ የሚገኘው የሀገራዊ ምክክር ሂደት ደግሞ ስር የሰደዱ ችግሮችን በዘላቂነት በመፍታት የኢትዮጵያን ከፍታ እንደሚያረጋግጥም እምነታቸውን ገልጸዋል። ከእንግሊዝ ሀገር የመጡት ተመካካሪ ኡስታዝ ሙክታር ጀማል፣ በታላቁ የህዳሴ ግድብ ጉብኝት ወቅት የተሰማቸውን ከፍተኛ ደስታ ገልጸዋል። የታሪካዊ ተቀናቃኞችን እኩይ ሴራ በድል አልፎ በኢትዮጵያውያን ጥረት ብቻ የተገነባውን ይህን ታሪካዊ ግድብ በዕድሜያቸው ማየት በመቻላቸው ታላቅ ኩራት እንደተሰማቸው በስሜት ገልጸዋል። ከካናዳ ቶሮንቶ የመጡት ተመካካሪ ጌትነት ሃይሉ በበኩላቸው፤ በውጭ ሀገር የሚገኙ ኢትዮጵያውያን የወር ደመወዛቸውን ሳይቀር በማዋጣት ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። በግድቡ ግንባታ ወቅት ዓለም አቀፍ ተቋማት ብድር በመከልከል ጫና ቢፈጥሩም፣ ኢትዮጵያውያን ግን በጋራ በመተባበር ግድቡን በራሳቸው አቅም መገንባታቸው ታሪካዊ ድል መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ለትውልድ ጠንካራ ሀገር ለማስተላለፍ የሚያስችላቸውን የምክክር ሂደት መሳተፍ በመቻላቸውም ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል። የምክክር ሂደቱ ውጤት አብሮነታችንን በማጽናት በተጠናከረ መልኩ በጋራ ለልማት መነሳሳት እንደሚቻል እምነታቸውን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ፍፁም አረጋ፤ በውጭ ሀገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ቦንድ በመግዛት፣ በስጦታ እና በዓለም አቀፍ መድረኮች ላይ ስለግድቡ በመከራከር ያደረጉትን አስተዋጽኦ አድንቀዋል። በአሁኑ ወቅት ግድቡ የኤሌትሪክ ሃይል ያልደረሳቸው ቀበሌዎች የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ እንዲሆኑ፣ ለከባድ ኢንዱስትሪዎች እና ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠሩን ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በንጋት ሐይቅ ዙሪያ የተፈጠሩትን ደሴቶች እና የቱሪዝም ፀጋዎች በመመልከት በቱሪዝም ኢንቨስትመንት እንዲሳተፉም ጥሪ አቅርበዋል።
ቀልጣፋ የአሰራር ስርዓት በመተግበር አልሚዎችን ወደ ሀገር ውስጥ ለመሳብ ተችሏል
Aug 9, 2026 567
ጋምቤላ፤ነሐሴ 3/2018 (ኢዜአ)፦ሀገሪቱ ያሏትን የኢንቨስትመንት እድሎች ለባለሀብቶች የማስተዋወቅ እና አገልግሎቶችን ቀልጣፋ የሚያደርጉ አሰራሮችን በመተግበር በርካታ አልሚዎችን ወደ ሀገር ውስጥ መሳብ መቻሉን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ገለጸ። የፌዴራል፣ የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የኢንቨስትመንት አስፈፃሚ አካላት በጋምቤላ ከተማ እያካሄዱት ባለው የጋራ ምክክር በ2018 በጀት ዓመት አፈፃፀምና በአዲሱ በጀት ዓመት እቅድ በመምከር የትኩረት አቅጣጫ አስቀምጠዋል። በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ዳጋቶ ኩምቤ በመድረኩ ላይ እንዳሉት የኢንቨስትመንት አማራጮችን በማስተዋወቅ አልሚዎችን ለመሳብ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስገኙ ነው። በዚህም በበጀት ዓመቱ ብቻ 528 የውጪ ሀገር ባለሃብቶች አዲስ የኢንቨስትመንት ፈቃድ መውሰዳቸውን ገልጸዋል። ''ኢንቨስት ኢን ኢትዮጵያ 2026 ፎረም’’ የኢንቨስትመንት ስምምነትንም የፈረሙ ሰባት ተቋማት 13 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ካፒታል ፈሰስ ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል። በቀጣይም የዲጂታል አገልግሎቱን በማስፋትና ቅንጅታዊ አሰራሮችን በማጠናከርና የኢትዮጵያን ኢንቨስትመንት ተመራጭነት ይበልጥ ለማሳደግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የኮሚሽኑ የስፔሻል ኢኮኖሚ ዞን ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር ዝናቡ ይርጋ በበኩላቸው፥ የኢንቨስትመንት አማራጮችን ወደ ውጤት በመቀየር የብልጽግና ጉዞ እውን ለማድረግ ቅንጅታዊ አሰራሩ ይጠናከራል ብለዋል። ለዚህም የመሰረተ ልማት አውታሮችን ተደራሽነት የማስፋትና የአሰራር ማእቀፎችን ማስፋት ላይ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የሚተገበር መሆኑን ተናግረዋል። የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው፥ ባለሃብቶች ለሚያጋጥማቸው ተግዳሮቶች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት ቅንጅታዊ አሰራሮችን ይበልጥ ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። የምክክር መድረኩ በ2018 እቅድ አፈፃፀምና በአዲሱ በጀት ዓመት ውይይት በማድረግ የትኩረት አቅጣጫ ያስቀመጠ ሲሆን ተሳፊዎች በዛሬው ዕለት ከጋምቤላ ክልል ርዕሰ መሰተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ጋር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሂደዋል። በቀጣይም የልማት ምልከታ የመስክ ጉብኝት በማካሄድ መርሃ ግብራቸውን እንደሚያጠናቅቁ ይጠበቃል።
በጉጂ ዞን በምርት ዘመኑ ከ231 ሺህ ኩንታል በላይ የቡና ምርት ለማእከላዊ ገበያ ቀረበ
Aug 9, 2026 585
አዶላ፤ ነሐሴ 3/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በዘንድሮው የምርት ዘመን ከ231 ሺህ ኩንታል በላይ የተፈጥሮ ጣእምና ጥራቱን የጠበቀ የቡና ምርት ለማእከላዊ ገበያ መቅረቡን የዞኑ ንግድ ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ የጉጂ ዞን በኢትዮጵያ ከሚገኙ የቡና አምራች አካባቢዎች መካከል በጥራትና በምርት መጠን በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀስ አካባቢ ነው፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ በከፍተኛ ዋጋ ከሚሸጡ የታጠቡና ያልታጠቡ የቡና አይነቶች መካከል የጉጂ ቡና ይጠቀሳል፡፡ በዞኑ የሚገኙ አነስተኛ አባወራ አምራቾች፣ የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበራትና ባለሀብቶች በቡና መልቀም፣ ማጠብና ማድረቅ ሂደት ላይ ባላቸው ልምድ ምክንያት የምርቱን ጥራት ለማስጠበቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዞኑ የተደረጉ የጥራት ቁጥጥር ስራዎች፣ የኮንትሮባንድ ንግድን የመግታት እርምጃዎችና አምራቾችን በቀጥታ ከማዕከላዊ ገበያ ጋር የማገናኘት አሰራር ምርቱ በጥራትና በስፋት ለገበያ እንዲቀርብ አግዟል፡፡ በዞኑ ንግድ ጽህፈት ቤት የእቅድና በጀት ባለሙያ አቶ ደረሰ ደንቆ በ2018 በጀት አመት ከዞኑ በጥራትና በብዛት የሚወዳደር የቡና ምርት ለማቅረብ የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውን አስታውሰዋል፡፡ በእስካሁኑ ክንውንም ከዞኑ ቡና አምራች ወረዳዎች የተሰበሰበ 231 ሺህ 190 ኩንታል የተፈጥሮ ጣእምና ጥራት ያለው ምርት ለማዕከላዊ ገበያ ቀርቧል ብለዋል፡፡ ከዚህ ውስጥ 174 ሺህ 100 ደረቅ እና 57 ሺህ 90 ኩንታል ታጥቦ የተቀሸረ የደረቅ ቡና ምርት እንደሆነም ገልጸዋል፡፡ በዞኑ የተቋቋሙ በርካታ የደረቅና የእሼት ቡና ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪዎች ቡናን በብዛትና በጥራት እያዘጋጁ በማቅረብ ላይ እንደሆኑም ጠቁመዋል፡፡ የጉጂ ቡና በጣእምና ጥራቱ ተመራጭና ተፈላጊ እየሆነ በመምጣቱ ከተለያዩ ቡና ላኪ ኩባንያዎች እውቅናና የምስክር ወረቀት መሰጠቱንም አስታውሰዋል፡፡ እውቅናው የዞኑ የተፈጥሮ ቡና ጣእምና ጥራቱን ሳይለቅ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ለማቅረብ መነሳሳት መፍጠሩንም ገልጸዋል፡፡ የዞኑ የቡና ልማት የሚከናወነው በተፈጥሮ ደኖች ጥላ ስር በመሆኑ ባለልዩ የተፈጥሮ ጣእም ባለቤት እንዲሆን ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ በዞኑ አዶላ ከተማ የተቋቋመው የቡና ጣእምና ቅምሻ ማእከል ለምርት ጥራትና አቅርቦት መሻሻል መነሳሳት ፈጥሯል ብለዋል፡፡ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ደስታ ገብረየሱስ በበኩላቸው መንግስት ለቡና ልማት የሰጠው ትኩረት ምርታማነትን በተሻለ እያሳደገ ነው ብለዋል፡፡ በዞኑ 13 ወረዳዎች በቡና ልማት ከተሸፈነው ከ187 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት አብዛኛው በተሻሻለ የቡና ተክል የለማ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በዞኑ ከሰብል ልማትና ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን ከ110 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በቡና ልማት መሳተፋቸውንም አስታውቀዋል፡፡ በዞኑ አዶላ ወረዳ አንፈራራ ቀበሌ በቡና ልማት የተሳተፉት አቶ ገመዳ ሀለኬ ለልማቱ ትኩረት መሰጠቱ ምርታችንን በማሳደግ ተጠቃሚ አድርጎናል ብለዋል፡፡ ነባሩን የቡና ልማት በተሻሻለ ዝርያ በመተካት ብዛትና ጥራት ያለው ምርት በመሰብሰብ ለገበያ እያቀረቡ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ የተሻሻለው የቡና ዝርያ ምርታማነትን ከማሳደግ ሌላ ብርድና በሽታ በመቋቋም የተሻለ መርት የሚሰጥ መሆኑም እንዲሁ።
በአፋር ክልል የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Aug 8, 2026 692
ሰመራ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦ በአፋር ክልል የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አወል አርባ ገለጹ። የአፋር ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 5ኛ የሥራ ዘመን፣ 10ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ ይገኛል። ርዕሰ መስተዳድር አቶ አወል አርባ የክልሉን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ለምክር ቤቱ ባቀረቡበት ወቅት እንደተናገሩት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ ናቸው። በተለይም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራትን ማከናወን የተቻለ ሲሆን፤ በመስኖ ልማትም 142 ሺህ 675 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎችና አትክልቶች መሸፈን መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም መሠረት በበጀት ዓመቱ ከ5 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰብ መቻሉን አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅት የተለያዩ የግብርና ግብዓቶች መሰራጨታቸውን አመልክተው፤ ከዚህ ውስጥም ከ47 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጉን ገልጸዋል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በክልሉ ያልለሙ መሬቶችን ወደ እርሻ ሥራ በማስገባት የአርብቶ አደሩና ከፊል አርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ማስቻሉንም ነው ያብራሩት። በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ከዚህ ቀደም ይስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን በማስወገድ በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከ16 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም አስረድተዋል። የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያን እስከ ታች ድረስ በማውረድና የንቅናቄ ሥራዎችን በማከናወን ከ405 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። ርዕሰ መስተዳድር አቶ አወል በሪፖርታቸው፤ በክልል ደረጃ 80 ሺህ 621 ዜጎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸውንም ነው ለምክር ቤቱ የገለጹት።
በሲዳማ ክልል የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማትን በማሻሻል ለሕዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Aug 8, 2026 647
ሀዋሳ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማትን በማሻሻል ለሕዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸው ተገለጸ። የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸሙን ገምግሟል። በመድረኩ የተገኙት የክልሉ የመንግሥት ረዳት ተጠሪ አቶ አሸናፊ ኤልያስ እንዳሉት፣ የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማትን በማሻሻል ለሕዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው። ከተማን ከወረዳና ከገጠር ቀበሌዎች የሚያገናኙ መንገዶችንና የአገልግሎት መስጫ ተቋማትን ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት መሰራቱን ጠቁመዋል። የክልሉ ከተሞች ለኑሮ፣ ለሥራና ለኢንቨስትመንት ምቹ እንዲሆኑ የኮሪደር ልማት ስራን በመስራት፣ የመኖሪያና የኢንቨስትመንት ቦታ በማቅረብ የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በከተሞችና በገጠር መካከል ያለውን የእድገትና የልማት ልዩነት ለማጥበብ በገጠር ኮሪደርና ሞዴል መንደሮችን የማስፋፋት ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አቶ አሸናፊ ተናግረዋል። የሲዳማ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብሩክ ሰለሞን በበኩላቸው፣ የክልሉ ከተሞች ደረጃውን በጠበቀ ፕላን እንዲመሩ ለማድረግ በተከናወነው ሥራ የ73 ከተሞች የፕላን ክለሳና አዲስ ፕላን የማዘጋጀት ሥራ መሰራቱን ጠቁመዋል። በከተሞች የአገልግሎት አሰጣጡን ከማሻሻል አኳያ በሐዋሳ በክልሉና በከተማ አስተዳደሩ «መሶብ» የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ወደ ስራ በማስገባት ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት መቻላቸውን ገልጸዋል። ይህን ለማስፋት በስድስት ከተሞች የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ማዕከላት ግንባታ ተጠናቆ የቁሳቁስ የማሟላት ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰው፣ በተያዘው የ2019 በጀት ዓመት ወደ ሥራ እንዲገቡ ይደረጋል ብለዋል። የወንዶገነት ወረዳ ኮንስትራክሽን ባለሥልጣን ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መልካሙ ኤርሚያስ እንዳሉት፣ በወረዳው በከተማና በገጠር መካከል ያለውን የልማት ልዩነት ለማመጣጠን እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። በወረዳው የገጠር ኮሪደር ልማትና ሞዴል የገጠር መንደሮችን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተከናወነ ተግባር 13 ሞዴል ቤቶችን መገንባት እንደተቻለ ገልጸዋል። ወንዶገነት በወሻ ከተማ አቅራቢያ ያሉ የተፈጥሮ ፍልውኃዎችን በአግባቡ አልምቶ የቱሪስት ፍሰቱንና ገቢን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። የሴክተሩ የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ ላይ የክልሉ አራት ዞኖች ዋና አስተዳዳሪዎች፣ የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ፣ የወረዳ አመራሮችና የሴክተሩ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል።
የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ አሲዳማ መሬትን የማከም ተግባር እያከናወነ ይገኛል
Aug 8, 2026 743
ቴፒ፤ ነሐሴ 02/2018 (ኢዜአ)፦ የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ የሚያስችል አሲዳማ መሬትን የማከም ተግባር እያከናወነ መሆኑን አስታወቀ። ማዕከሉ በምርምር አዳዲስ ዝርያዎችን ከማውጣትና ከማላመድ ባሻገር የአፈር አሲዳማነት ቁጥጥርና ማከም ተግባራትን በማከናወን ለአርሶ አደሮች ችግር ፈቺ መፍትሔዎችን እያቀረበ መሆኑን ገልጿል። የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር ደረጀ ቱሉ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ የአርሶ አደሩን የግብርና ሥራ ውጤታማነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት ምርታማነትን የሚቀንሱ ምክንያቶችን በጥናት ተከታትሎ ማስወገድ ይገባል። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችና በጋምቤላ ክልሎች በአሲዳማነት የተጠቃ ሰፊ ማሳ መኖሩን ጠቅሰዋል። "ይህም ምርታማነትን በመቀነስ በአርሶ አደሩ ላይ የሚያሳድረውን አሉታዊ ተጽዕኖ ለመግታት አሲዳማ መሬትን የማከም ሥራ እየሠራን ነው" ብለዋል። በዘንድሮው ዓመት በክልሉ ከ100 ሄክታር በላይ ማሳ የማከም ተግባር መከናወኑን ገልጸው ከዚህ ውስጥ በየኪ ወረዳ 22 ሄክታር ማሳ ምርት አያያዝ ውጤታማ ሆኖ መገኘቱን አስረድተዋል። ማዕከሉ አሲዳማ አፈርን በመመርመር በኖራ፣ በቨርሚ ኮምፖስት እንዲሁም በኖራና በተፈጥሮ ኮምፖስት ቅይጥ የማከም ሥራ የሚሠራ ሲሆን፣ በቀጣይም ይህን ተግባር በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ይሠራል ብለዋል። የአፈር አሲዳማነት በይበልጥ በበቆሎ ምርት ላይ ጉዳት የሚያደርስ በመሆኑ ከአንድ ሄክታር ከ20 ኩንታል ያነሰ ምርት እንዲሰጥ እንደሚያደርግ በማዕከሉ የአፈር ለምነት ተመራማሪ ሙሉሰው ወዳጆ ተናግረዋል። ዝናብ በሚበዛባቸው አካባቢዎች ጎልቶ የሚታየው አሲዳማ መሬት ከታከመ በኋላ ከ70 ኩንታል በላይ የበቆሎ ምርት ወደ መስጠት ደረጃ ተመልሶ እንደሚያገግም ገልጸዋል። የየኪ ወረዳ ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ኅብረት ሥራ ጽሕፈት ቤት የአዝርዕትና ሰብል ልማት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ይርጋለም አሰፋ በዞኑ በቆሎ በተስማሚነት የሚለማ ቢሆንም፣ በአሲዳማ አፈር ስለሚጠቃ ምርታማነቱ አነስተኛ መሆኑን ጠቁመዋል። በምርምር ማዕከሉ የታከመው ማሳ ያመጣውን ውጤት በቀጣይ በሌሎች ማሳዎች ወደተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ለማስፋት ትኩረት አድርገው እንደሚሠሩ ገልጸዋል። ከአካባቢው አርሶ አደሮች መካከል የአዲስዓለም ቀበሌ አርሶ አደር መሐመድ ሰኢድ እና ሰሎሞን ኃይሌ፣ የግብርና ምርምሩ ማሳቸውን በኖራ አክሞ ተስፋቸው እንዳለመለመ ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በቆሎ ሲዘሩ ግማሹ ሳይበቅል የሚቀርበትና የበቀለውም እየቀጨጨ የሚበላሽበት ሁኔታ ይገጥማቸው እንደነበር ገልጸው አሁን ላይ ማሳው ታክሞ የዘሩት በቆሎ ምርት አያያዝ ከቤተሰብ ፍጆታ ተርፎ ለገበያ መብቃት የሚችል መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም ሌሎች ማሳዎቻቸውን በማሳከም ምርታማነታቸውን ለማሳደግ ጠንክረው እንደሚሠሩም አርሶ አደሮቹ ተናግረዋል። በየኪ ወረዳ አዲስ ዓለም ቀበሌ 22 ሄክታር አሲዳማ መሬት በኖራ ታክሞ 86 አርሶ አደሮች በኩታ ገጠም ያለሙት የበቆሎ ማሳ ውጤታማነት ተሞክሮ ለሌሎች እንዲጋሩ እየተደረገ መሆኑም ተመላክቷል።
የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽንና የሪፖርታጅ ግሩፕ የልማት ትብብር የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ዘርፉን ለማዘመን ተጨማሪ አቅም ይፈጥራል
Aug 8, 2026 602
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽንና የሪፖርታጅ ግሩፕ የልማት ትብብር የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ዘርፉን ለማዘመን ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር መሆኑን የመከላከያ ሚኒስትር ዴኤታ ማርታ ሉዊጂ ገለጹ። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ከዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ ሪፖርታጅ ግሩፕ ጋር በመተባበር በአዲስ አበባ ሁለገብ የመኖሪያና የንግድ ሕንፃ ለመገንባት የልማት አጋርነት ፕሮጀክት ይፋ አደረጉ። የመከላከያ ሚኒስትር ዴኤታ ማርታ ሉዊጂ በዚህ ወቅት፣ አጋርነቱ የተቋማቱን ስትራቴጂያዊ የልማት አጋርነት በማጠናከር የኢትዮጵያና ዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ ትብብርን የሚያሳድግ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የሀገራቱን ጠንካራ ስትራቴጂያዊ አጋርነት ወደ ላቀ ምዕራፍ ለማሸጋገር የሚያስችል ጭምር እንደሆነም ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ ዘመናዊ ከተማን በመገንባት የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ለማጠናከር ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አመልክተዋል። የፋውንዴሽኑና የሪፖርታጅ ግሩፕ ትብብርም ዓለም አቀፍ አልሚዎች ኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት መዳረሻ የስበት ማዕከል እያደረጓት እንደሚገኝ ማሳያ ነው ብለዋል። የሪፖርታጅ ግሩፕ ሊቀመንበር አሪፍ ኢስማኤል በበኩላቸው ፕሮጀክቱ በሀገራቱ መካከል ያለውን ሁለንተናዊ የልማት ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑን ገልጸዋል። የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሜጀር ጄኔራል ደረጀ መገርሳ፣ ፕሮጀክቱ ከአዲስ አበባ ፈጣን የከተሜነት ዕድገት ጋር የሚመጣጠን ዘመናዊ ግንባታ እንደሚሆን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ ለሠራዊቱ የመኖሪያ ቤት ፍላጎት ለማሟላት ተጨማሪ የገቢ አቅም የሚገነባ መሆኑን አመልክተዋል። የሪፖርታጅ ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሐናን አሕመድ ኑር እንዳሉት፤ በአፍሪካ ሕብረት ዋና መሥሪያ ቤት ፊት ለፊት በ23 ሺህ ካሬ ሜትር የሚገነባውን ፕሮጀክት በሦስት ዓመታት ጊዜ ለማጠናቀቅ ይሰራል ብለዋል። ሕንፃው 1 ሺህ 86 ስቱዲዮ፣ ባለአንድና ባለሁለት መኝታ የመኖሪያ አፓርታማ፣ የንግድ ሱቆች፣ ጂምናዚየም፣ መዋኛ ገንዳ፣ የስፖርት ማዘውተሪያና ሌሎች ዘመናዊ አገልግሎቶችን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱም በመኖሪያና በንግድ ልማት ብቻ ሳይወሰን ለኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ዘርፍ ዘመናዊነት፣ የሥራ ዕድል ፈጠራና ለኢንቨስትመንት መስፋፋት አዲስ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
በሀገሪቱ እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ በትብብርና በቅንጅት መስራት ይገባል
Aug 8, 2026 614
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦ የኢንቨስትመንቱን ዘርፍ በማጠናከር እንደ ሀገር እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ የትብብርና የቅንጅት ስራዎች ሊጠናከሩ እንደሚገባ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። በሀገር አቀፍ ደረጃ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተከናወኑት ሥራዎች ከ4 ነጥብ 44 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን አስታውቋል። የፌዴራል፣ የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የኢንቨስትመንት አስፈጻሚዎች የጋራ ሀገራዊ የምክክር መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ መካሄድ ጀምሯል። ርዕሰ መስተዳድሯ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ እንደ ክልል ብሎም እንደ ሀገር ሰፊ የኢንቨስትመንት አማራጮች አሉ፤ እነዚህንም ልማት ላይ ማዋል ይገባል። በዚህም እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ በፌዴራልና በክልሎች የተጀመሩ የትብብርና ቅንጅታዊ አሠራሮች ይበልጥ ሊጠናከሩ ይገባል ብለዋል። በክልሉ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በኢንቨስትመንት ዘርፉ በተከናወኑት ሥራዎች በርካታ ባለሀብቶች ወደ ክልሉ በመግባት በዘርፉ እየተሳተፉ እንደሚገኙና ተጨባጭ ውጤትም እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በቀጣይም በክልሉ ያሉትን የግብርና፣ የማዕድን፣ የቱሪዝምና ሌሎች የኢንቨስትመንት አማራጮች ምቹ በማድረግ ለዘርፉ መጠናከር የክልሉ መንግሥት በትኩረት እንደሚሠራ ነው ያረጋገጡት። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ዳጋቶ ኩምቤ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ ኮሚሽኑ የተጣለበትን ሀገራዊ ኃላፊነት ለመወጣት ባከናወናቸው ተግባራት አበረታች ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዘርፉ በተከናወኑት ሥራዎች ከ4 ነጥብ 44 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን ጠቁመዋል። ይህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ8 ከመቶ በላይ ብልጫ ያለው መሆኑን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ አበረታች ውጤቶችን ማስመዝገብ የተቻለው የፌዴራልና የክልል ባለድርሻ አካላት ያደረጉት ያልተቆጠበ የተቀናጀ ጥረት ውጤት መሆኑንም ተናግረዋል። በቀጣይም የትብብርና የቅንጅታዊ ሥራዎችን በማጠናከር በዘርፉ የተገኙትን ስኬቶች ይበልጥ ለማስፋት እንደሚሠራ ምክትል ኮሚሽነሩ ገልጸዋል። የጋምቤላ ክልል ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሎው ኡቡፕ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በክልሉ ባሉት የኢንቨስትመንት አማራጮች የባለሀብቶች ተሳትፎ እንዲጠናከር በማድረግ ረገድ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል ብለዋል። በቀጣይም ከምክክር መድረኩ የሚገኙ ተሞክሮና ልምዶችን በማስፋት ለዘርፉ ውጤታማነት በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል። ከዛሬ ጀምሮ ለሁለት ቀናት በሚቆየው የምክክር መድረክ የፌዴራል፣ የክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች የኢንቨስትመንት አስፈጻሚዎች በ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸምና በአዲሱ በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ በመወያየት የጋራ አቅጣጫ ያስቀምጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።