ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በሲዳማ ክልል የህዝብን የልማት ጥያቄ የመመለሱ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Sep 3, 2026 178
ሀዋሳ፣ ነሀሴ 28/2018 (ኢዜአ) በሲዳማ ክልል የሕዝቡን የልማት ጥያቄ የሚመልሱ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ አስታወቁ። በርዕሰ መስተዳድሩ የሚመራ የክልሉ ከፍተኛ አመራር ቡድን በምስራቃዊና ማዕከላዊ ሲዳማ ዞኖች እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን ተዘዋውሮ ተመልክቷል። ርዕሰ መስተዳድሩ ደስታ ሌዳሞ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ የሕዝቡን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ የመመለሱ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል። በምስራቃዊ ሲዳማ ዞን በንሳ ወረዳ ዳዬ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ሥራ ከተማዋን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ እና ተመራጭ እንደሚያደርጋት ገልጸዋል። የኮሪደር ልማት ሥራው በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንደሚበቃም አክለዋል። ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የሚነሱ ጥያቄዎችን ለመመለስ ታስቦ እየተገነባ የሚገኘውን የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ለማጠናቀቅም ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የልኡካን ቡድኑ የአርቤጎና እና የቡራ ወረዳዎችን የሚያገናኘውና በሎጊታ ወንዝ ላይ እየተገነባ ያለው የባሬ ድልድይ እንዲሁም የቡራ ወረዳ የአስተዳደር ጽሕፈት ቤት ሕንፃ ግንባታ በዚሁ ወቅት ከጎበኙዋቸው የልማት ስራዎች መካከል ይጠቀሳሉ። የክልሉ መንግሥት የሕዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ እና የልማት ጥያቄዎችን የሚመልሱ ፕሮጀክቶችን እውን የማድረጉ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ርዕሰ መስተዳድሩ ገልጸዋል። በቡራ ወረዳ እየተገነባ የሚገኘው የአስተዳደር ሕንፃም የመንግሥት አገልግሎትን ምቹና ቀልጣፋ በሆነ መንገድ ለመስጠት እንደሚያስችል ነው ያመለከቱት። በቡራ ወረዳ ዳለቻ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ባንጫ ባዲሶ በበኩላቸው፣ የአርቤጎና እና ቡራ ወረዳዎችን የሚያገናኘው የባሬ ድልድይ መሠራቱ ቀደም ሲል ወንዙን ለመሻገር ይገጥም የነበረውን ችግር እንዳስቀረላቸው ተናግረዋል። ወንዙ በሚሞላበት ወቅት በርካቶች ለመሻገር ሲሞክሩ በደራሽ ውኃ ይወሰዱ እንደነበር አስታውሰው፣ የድልድዩ ግንባታ ትልቅ እፎይታ እንደሰጣቸው ገልጸዋል። ሌላው የአርቤጎና ወረዳ ሚቂቾ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ፌኦ ሲዱ በበኩላቸው፣ የድልድዩ መገንባት ምርቶቻቸውን ወደ ገበያ ለማውጣትና የሚፈልጉትን ሸምተው ለመመለስ ይገጥማቸው የነበረውን ችግር እንደፈታላቸው ገልጸዋል። በጉብኝቱ ላይ የክልሉ፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሮች ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
መንግሥት የዜጎችን ኑሮ ማሻሻልና ዘላቂ ብልጽግናን ማረጋገጥ ቀዳሚ አጀንዳው አድርጓል - የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
Sep 3, 2026 186
አዲስ አበባ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፦ መንግሥት የዜጎችን ኑሮ ማሻሻልና ዘላቂ ብልጽግናን ማረጋገጥ ቀዳሚ አጀንዳው ማድረጉን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለጸ። አገልግሎቱ መንግሥት ሃገራዊ ሪፎርሞችን በመተግበር የሕዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የገባውን ቃል ወደ ተግባር እየለወጠ ይገኛል ብሏል። ኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥና የዜጎቿን ሕይወት ከፍ ለማድረግ በምታደርገው ያልተቋረጠ ርብርብ፣ የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ የሚያበስሩ ታሪካዊ ምዕራፎች እውን እየሆኑ ይገኛሉ ብሏል። መንግሥት ሕዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ስልታዊ ፖሊሲዎችን በመንደፍና በመተግበር በኢኮኖሚውና በማኅበራዊው ዘርፍ ተጨባጭ ለውጦችን በማስመዝገብ ላይ እንደሚገኝ ገልጿል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዛሬ ይፋ የተደረገው በኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እና በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን (IFC) መካከል የተደረሰው ታሪካዊ ስምምነት የዚህ አበይት ርዕይ አንዱ ማሳያ ነው ሲልም አገልግሎቱ አብራርቷል። በ100 ቢሊየን ብር ካፒታል የሚቋቋመውና ዓለም አቀፍ አጋርነትን ያካተተው የቤት መግዣ ብድር መልሶ ማጠናከሪያ ኩባንያ፣ በባንክ ዘርፍ ያለውን የጥሬ ገንዘብ ፍሰት አለመመጣጠን በመቅረፍ ለዜጎች አስተማማኝ የፋይናንስ አቅርቦት ይፈጥራል ብሏል። አገልግሎቱ ይህ ታሪካዊ ስምምነት መንግሥት በተመጣጣኝ ዋጋ የኢትዮጵያውያንን ክብር የጠበቁ 1.5 ሚሊየን ቤቶችን ለማቅረብ ያስቀመጠውን ግብ በግንባር ቀደምትነት የሚያሳካ መሆኑን ገልጿል። ስምምነቱ የዜጎችን የቤት ባለቤትነት ፍላጎት እውን በማድረግ ረገድ የሚታዩ ማነቆዎችን በመስበር፣ የበርካቶችን የዕለት ተዕለት ሕይወትና ማኅበራዊ ደኅንነት በአስተማማኝ ሁኔታ የሚያሻሽል የመንግሥት ቁርጠኝነትን ያረጋገጠ ቁልፍ ርምጃ መሆኑንም ጠቅሷል። ይህ ስኬት ብቻውን የቆመ አይደለም፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በኢኮኖሚ ማሻሻያ፣ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና በሜጋ ፕሮጀክቶች የተመዘገቡት የኢትዮጵያን የማንሰራራት ድሎች ቀጣይ ምዕራፍ አካል ነው። የመደመር መንግሥት የግል ዘርፉን ተሳትፎ በስፋት በማካተትና የገበያ ሥርዓቱን በማዘመን አገራዊ የኢኮኖሚ አቅምን ማጠናከር የልማት ጉዞው መሠረት አድርጎ ቀጥሏል። እንደ ሀገር እየተመዘገበ ካለው ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ጋር ተያይዞ በሚፈጠር የዋጋ ግሽበት አነስተኛ ገቢ ያላቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ላይ የሚደርሰውን ተጋላጭነት ለመቀነስ፣ መንግሥት በቢሊዮኖች የሚቆጠር በጀት በመመደብ በነዳጅ፣ በመሠረታዊ ፍጆታዎች እና በግብርና ግብአቶች ላይ ከፍተኛ ድጋፎችን እያደረገ ይገኛል። ከዚህ የዕለት ኑሮ ማቃለያ ሥራ ባሻገር የዜጎችን ኑሮ በዘላቂነት ማሻሻልና ብልጽግናን ማረጋገጥ ቀዳሚ አጀንዳው አድርጎል። በዚህም ቃል በተግባር እየተለወጠ ፈጣን፣ ጠንካራ እና ሁሉንም ያካተተ ኢኮኖሚ የመገንባት ጽኑ ፍላጎቱ በሁሉም መስክ በተግባር እየተፈጸመ ቀጥሏል ብሏል።
የሸገር ከተማ አስተዳደር አርሶ አደሮችን ማዕከል ያደረገ ዘመናዊ ከተማ ለመገንባት የሚያስችሉ ተግባራት እያከናወነ ነው
Sep 3, 2026 109
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፡- የሸገር ከተማ አስተዳደር ዘመናዊና ውጤታማ ከተማ ለመገንባት በሚያደርገው እንቅስቃሴ አርሶ አደሮችን ማዕከል ያደረጉ ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ የከተማዋ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) ገለጹ። በተለያዩ ሥነ-ሥርዓቶች ሲከበር የቆየው የሸገር ከተማ አስተዳዳር የአርሶ አደሮችን ቀን ዛሬ በፓናል ውይይትና የከተማዋ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮችን እውቅና በመስጠት ዛሬ ተጠናቋል። ዛሬ በዓድዋ ድል መታሰቢያ አዳራሽ በተካሄደ የፓናል ውይይት "የመደመር መንግሥት እይታ እና የአርሶአደሮች ተጠቃሚነት" በሚል ርዕስ ሰነድ ቀርቦ ውይይት የተደረገበት ሲሆን፣ ለሞዴል አርሶ አደሮችም የእውቅናና የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቷል። የሸገር ከተማ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ፤ በከተማዋ ባለፉት ዓመታት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ አሳታፊ ልማትን ለማስፈንና ውጤታማ የኢኮኖሚ ሽግግር ለማምጣት በተከናወኑ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ተመዝግበዋል። በተለይም ጠንካራ ከተማን ለመገንባት አርሶ አደሩን ማሰልጠን፣ የከተማ ግብርናን ማዘመንና አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ማድረግ ለሀገር ኢኮኖሚ መሰረት ስለሆነ ጠንካራ ስራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል። የከተማዋን የኢኮኖሚ ዕድገትና ግንባታ እውን ለማድረግ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ ላይ በትኩረት እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የሸገር ከተማ በአዲስ መልኩ ከመደራጀቱ በፊት በክረምት ወቅት ይለማ የነበረው 50 ሺሕ ሄክታር መሬት ብቻ እንደነበር ያስታወሱት ከንቲባው፣ በአሁኑ ወቅት የማልማት አቅሙን ወደ 95 ሺሕ ሄክታር ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል። በተጨማሪም ቀደም ሲል ከአንድ ሄክታር መሬት በሽያጭ ወይም በምርት ደረጃ በሰፊው ይገኝ የነበረው 37 ኩንታል አማካይ ምርት፣ በአሁኑ ወቅት ወደ 45 ኩንታል ማደጉን ገልጸዋል። ለአርሶ አደሩ የሚሰጡ ሥልጠናዎችን፣ የግብዓት አቅርቦትና የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሳደግ ግብርናውን ከባህላዊ ወደ ዘመናዊ ማሸጋገር ተችሏል ያሉት ከንቲባው፤ ይህም ምርትና ምርታማነትን ከመጨመር ባለፈ አርሶ አደሮች ለገበያ በማቅረብ ሀብት እንዲያፈሩ ማስቻሉን ገልጸዋል። በሌማት ትሩፋትና በቤተሰብ ብልጽግና ረገድም ተጨባጭ ውጤት መገኘቱን የጠቀሱት ከንቲባው፤ በተለይም የግብርና ሥርዓቱን ወደ እንስሳት እርባታ በማሸጋገር አርሶ አደሩ ይበልጥ ተጠቃሚ እየሆነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። አክለውም ሸገር ከተማ ከተመሠረተ ወዲህ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የገበያ ትስስርን የሚያጠናክሩ የማዕከላዊ ገበያዎችና የመሠረተ ልማት ዝርግታዎች በመከናወናቸው የሕዝቡ ተጠቃሚነት እየተረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ እውቅና ከተሰጣቸው አርሶ አደሮች መካከል የፉሪ ክፍለ ከተማ ነዋሪው አቶ በቀለ ደሜ፣ ሸገር ከተማ እንደ አዲስ ከመደራጀቱ በፊት በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ያመርቱ እንደነበርገልጸዋል። ባለፉት ሦስት ዓመታት በተደረገላቸው የስልጠና፣ የቴክኖሎጂና የግብዓት አቅርቦት ድጋፍ በእንስሳት እርባታና በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተው ኑሯቸውን ከማሻሻል ባሻገር ለበርካቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን አስታውቀዋል። አርሶ አደር እንግዳ አርጋው በበኩላቸው፣ በተለይም የመስኖ ድንችና ስንዴን በስፋት በማምረት ከፍተኛ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። አስተዳደሩ ከጎናቸው በመቆም አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረጉ ውጤታማ መሆን መቻላቸውንም አስታውቀዋል። አርሶ አደሮቹ አክለውም፣ በቀጣይ በግብርናው ዘርፍ ተግተው በመስራት ወደ ኢንቨስትመንት ለመሸጋገር ዕቅድ እንዳላቸው በመጠቆም፣ በዚህም ሀገራዊ የኢኮኖሚ እድገት ውስጥ የራሳቸውን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በጋምቤላ ክልል የሰብአዊ ድጋፎችን በእራስ አቅም ለመሸፈን ለተያዘው ግብ መሳካት የባለድርሻ አካላት ትብብር ይጠናከራል
Sep 3, 2026 164
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ) ፡-በጋምቤላ ክልል ሰብአዊ ድጋፎችን በራስ አቅም ለመሸፈን ለተያዘው ግብ መሳካት የባለድርሻ አካላት ትብብር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) ገለጹ። ተረጅነትን ለማስቀረት እየተከናወኑ ባሉት ስራዎችና በቀጣይ የበጋ መስኖ የግብርና ልማት ዙሪያ ያተኮረ የንቅናቄ ውይይት መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተካሄዷል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፣ ለሚከሰቱ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች ሰብአዊ ድጋፎችን በራስ አቅም ለመሸፈን ባለድርሻ አካላትን ያሳተፉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በክልሉ ከተረጅነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የተቀየሱ እቅዶችን ውጤታማ ለማድረግ ያለውን ሰፊ የመሬትና የውሃ ሀብት ካለው የሰው ኃይል ጋር አቀናጅቶ ለመጠቀም እየተሰራ ይገኛል ነው ያሉት። በዚህም ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ ለሚያጋጥሙ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች በራስ አቅም ሰብአዊ ድጋፍ ለመስጠት የመጠባበቂያ የሰብል ምርትና የበጀት ፈንድ ላይ ትኩረት መሰጠቱን አስረድተዋል። ምርታማነትን ከማሳደግ ጎን ለጎን ወቅት ጠብቆ ከማምረት ለመውጣት ለተነደፈው የበጋ ወራት የመስኖ ልማት ከወዲሁ አስፈላጊውን ዝግጅት ማድረግ እንደሚገባም አሳስበዋል። ለዘርፉ ስኬታማነት በጋራ መረባረብ የሚገባ ሲሆን የግብአትና የባለሙያ ድጋፍ ለአርሶ አደሩ ለማቅረብ ከመቼውም ጊዜ በላይ መስራት እንደሚገባ ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ አክለው ገልጸዋል። በክልሉ ሰብአዊ ድጋፎችን በራስ አቅም ምላሽ ለመስጠት የ400 ሚሊዮን ብር የመጠባበቂያ ፈንድ እቅድ ተነድፎ ንቅናቄ መጀመሩንም አስረድተዋል። በብልጽግና ፓርቲ የጋምቤላ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አሸኔ አስቲን በበኩላቸው፣ እንደ ሀገር ከተረጅነት ለመውጣት እየተተገበረ ላለው ኢኒሼቲቭ ውጤታማነት የመንግስትም ሆነ የድርጅቱ አመራሮች በቁርጠኝነት መስራት ይገባል ብለዋል። በተለይ ሕብረተሰቡ ምርታማነቱን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ እንዲችል ያልተቆጠበ የድጋፍና የክትትል ስራዎችን ማከናወን የግድ እንደሚለው ነው የተናገሩት። በንቅናቄ የውይይት መድረኩ ላይ የመንግስትና የድርጅት አመራሮች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በጋምቤላ ክልል ተግባራዊ የተደረገው የሩዝ ልማት ኢኒሼቲቭ ውጤታማ እየሆነ መጥቷል
Sep 3, 2026 92
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል ተግባራዊ የተደረገው የሩዝ ልማት ኢኒሼቲቭ ውጤታማ እየሆነ መምጣቱን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። በኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የምግብ ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመተካትና የአርሶ አደሩን ገቢ ለማሳደግ ከተቀመጠው ስትራቴጂካዊ የግብርና ምርቶች መካከል ሩዝ አንዱና ዋነኛው ነው:: ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሩዝ ልማት በሀገሪቱ የግብርና ፖሊሲ ውስጥ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት በስፋት እየተከወነ ይገኛል:: በተለይ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ከውጭ የሚገባውን የሩዝ ምርት በአገር ውስጥ ለመተካት በተያዘው አገራዊ አቅጣጫ መሠረት ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል። የጋምቤላ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንድሩው ቱት ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ክልሉ ለሩዝ ልማት አመቺ በመሆኑ አርሶ አደሩ በዘርፉ ለመሰማራት የሚያሳየው ፍላጎት እየጨመረ መጥቷል። በተለይም በአኝዋህ እና በማጃንግ ዞኖች በሩዝ ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች አበረታች ውጤት እያገኙ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የተገኘውን አዎንታዊ ውጤት በሌሎች የክልሉ አካባቢዎች በማስፋት፣ አገራዊ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅት የሩዝ መፈልፈያ ማሽኖችን እና ምርታማ የሆኑ አዳዲስ የሩዝ ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል። እንደ ሩዝ ልማት ያሉ የተመረጡ የግብርና ኢኒሺቲቮች የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር፣ አርሶ አደሩ ምርቱን ለገበያ በማቅረብ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆን ማድረጋቸውንም አክለው ገልፀዋል። የአቦቦ ወረዳ አርሶ አደር እስማኤል ሁሴን፤ በአካባቢያቸው ሩዝ በማልማት በሄክታር እስከ 60 ኩንታል ምርት ማግኘት መቻላቸውን ገልፀዋል። በመሆኑም በሩዝ ልማት ዙሪያ የሚደረገውን ድጋፍ አጠናክሮ በመቀጠል አካባቢው ያለውን እምቅ ተፈጥሮአዊ ሀብት በአግባቡ መጠቀም እንደሚገባ ጠቁመዋል። አርሶ አደሩ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ በማምረት ተጠቃሚ እየሆነ እንደሚገኝ የገለፁት ደግሞ በዲማ ወረዳ የኮይ ቀበሌ የልማት ጣቢያ ባለሙያ አቶ ተረፈ ታፈሰ ናቸው።
በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ ውህደትን ማፋጠን ለአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ትግበራ እና ለተቀመጡ ግቦች መሳካት ጉልህ አስተዋጽኦ አለው-ዋምኬሌ ሜኔ
Sep 3, 2026 136
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፦በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ ውህደትን ማፋጠን ለአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ትግበራ እና ለተቀመጡት ግቦች መሳካት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለው የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ዋና ፀሀፊ ዋምኬሌ ሜኔ ገለጹ። የአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ የንግድ ሚኒስትሮች ስብሰባ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ዋና ጸሐፊ ዋምኬሌ ሜኔ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ የአፍሪካን አህጉራዊ ውህደት ማጠናከር፣ የምርት አቅምን ማሳደግ፣ንግድን ማብዛትና ማስፋፋት፣ እንዲሁም የተቋማትን አቅም ማጠናከር እጅግ አስፈላጊ ናቸው። ስብሰባው አፍሪካ ወደ ጥልቅ ውህደት በፍጥነት እየተጓዘች ባለችበት ወቅት የሚካሄድ መሆኑንም ገልጸዋል። በአህጉሪቱ ውስጥ ትኩረቱ ከድርድር ወደ አፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና በተግባር ወደ መፈጸምና ውጤት ወደ ማምጣት እየተሸጋገረ መሆኑንና አስፈላጊ የነበሩት ሁሉም ፕሮቶኮሎች መጠናቀቃቸውን ጠቁመዋል። እነዚህን ፕሮቶኮሎች በፍጥነት በማጠናቀቅ ለአህጉር አቀፍ ንግድ ጠንካራ የሕግ መሠረት መጣሉንና ተለዋዋጭ አህጉራዊ ገበያ ለመፍጠር ዝግጅት መደረጉን ጠቅሰዋል። በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ ውህደትን ማሳደግ የአህጉራዊ ጥረቱ አስፈላጊ አካል መሆኑን ጠቅሰው የአፍሪካ የረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ተስፋ እውን የሚሆነው ችግሮችን በቆራጥነት በመጋፈጥና እርምጃዎችን በመውሰድ መሆኑን ገልጸዋል። ኢኮኖሚዎችን ለማዋቀር፣ ኢንዱስትሪያዊ ልማትን ለማፋጠን፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠር እና የአፍሪካን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ለማጠናከር ቆራጥ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣናን ለማሳካት እድል እንደሚሰጥ ጠቁመዋል። የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣናን በተግባር የሚያስፈጽሙ አገራት 1.4 ቢሊዮን ሕዝብ ያለበትን እና በአጠቃላይ 3.4 ትሪሊዮን የአሜሪካ ዶላር ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) ያለውን ሰፊ ገበያ የማግኘት ዕድል እንደሚኖራቸው አመላክተዋል። በ2024 እ.ኤ.አ. የአፍሪካ አህጉር ውስጥ ንግድ 220 ቢሊዮን ዶላር መድረሱ የተመዘገበ ሲሆን፣ የዚህ ንግድ ትልቁ ድርሻም በኢንዱስትሪ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። ይህም የሚያበረታታ መሆኑን ገልጸው አፍሪካ እሴት በተጨመረባቸው ምርቶች ላይ የበለጠ እየነገደችና ባልተዘጋጁ ጥሬ ዕቃዎች ላይ የምታደርገው ንግድ እየቀነሰ መምጣቱን የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሰዋል። በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ ውህደትን ማፋጠን ለቀጠናው ሀገራት ብቻ ጠቃሚ ሳይሆን፣ ለአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጠና ትግበራ እና ለተቀመጡት ግቦች መሳካት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል። የተሻለ ትስስር ያለው ቀጣና፣ የበለጠ ቀልጣፋ ድንበሮች፣ ጠንካራ የምርት አቅም እና እየሰፋ የሚሄድ ቀጣናዊ የእሴት ሰንሰለት በመፍጠር የአፍሪካን አንድ የጋራ ገበያ እንደሚያጠናክር ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ ስኬት ቁርጠኛ ናት
Sep 3, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ ስኬት እና ለሁሉም ተሳታፊ ሀገራት ተጨባጭ ውጤት እንዲያመጣ ገንቢ ሚና ለመጫወት ቁርጠኛ መሆኗን የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ ታዜር ገብረእግዚአብሔር ገለጹ። የአፍሪካ ቀንድ ኢኒቬቲቭ የንግድ ሚኒስትሮች ስብሰባ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ ታዜር ገብረእግዚአብሔር በዚሁ ወቅት እንዳሉት ስብሰባው የቀጣናዊ ውህደትን ወሳኝ ጠቀሜታ ያሳያል ብለዋል። የቀጣናው ሀገራት በጂኦግራፊ፣ በታሪክ፣ በባህል እንዲሁም እየጨመረ በመጣው የጋራ የኢኮኖሚ ፍላጎት የተሳሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። የበለጠ ጥልቅ የቀጣናዊ ውህደት ሂደት ፈጣን ኢኮኖሚያዊ ዕድገትንና የሥራ ዕድል ፈጠራን የማፋጠን መንገድ ብቻ ሳይሆን፣ የጋራ የመቋቋም አቅም እና የመረጋጋት መሠረት መሆኑን አንስተዋል። የአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጠና ራዕይን ወደ ተጨባጭ እውነታ ለመቀየር ቁልፍ መንገድ ነው ብለዋል። ኢኒሼቲቩ ኢንቨስትመንቶችን ለማስተባበር፣ ፖሊሲዎችን ለማጣጣም እና ንግድንና ትስስርን የሚያደናቅፉ ማነቆዎችን ለመፍታት የተቀናጀ ማዕቀፍ እንደሚሆን አመላክተዋል። በዚህ ኢኒሼቲቭ አማካኝነት መንገዶች፣ ድንበሮችና የንግድ ኮሪደሮችን ከማሻሻል ባለፈ፣ መተማመንን የሚገነባ፣ ተቋማትን የሚያጠናክርና ለሕዝቦቻችን ዕድሎችን የሚፈጥር ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ቀንድ ኢኒሼቲቭ ስኬት ያላትን ጽኑ ቁርጠኝነት እንደምትቀጥልም አረጋግጠዋል። ለዚህም ቀጣናዊ ውህደትን በልማት ስትራቴጂ ማዕከል በማድረግ ለቀጣናዊ ኮሪደሮችና ንግድን ማመቻቸት የሚያገለግሉ መሠረተ ልማቶች ከጎረቤት ሀገራትና ከአጋሮቻችን ጋር በቅርበት በመሥራት ከፍተኛ ጥረት ማድረጓን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ከገንዘብ ድጋፍ ባለፈ ፖለቲካዊና ቴክኒካዊ ተሳትፎ እያደረገች መሆኑን ጠቅሰው፤ ኢኒሼቲቩ ለሁሉም ተሳታፊ ሀገራት ተጨባጭ ውጤት እንዲያመጣ ውይይትን በማስፋፋት፣ ፖሊሲዎችን በማጣጣምና ልምዶችን በመለዋወጥ ገንቢ ሚና ለመጫወት ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ከቀጣናዊ ውህደት ዓላማዎች ጋር በቅርበት የተሳሰረ መሆኑን አመላክተዋል። ኢትዮጵያ የንግድ ስርዓቷን እና የጉምሩክ አሠራሯን ለማዘመን፣ የንግድ ሥራ አካባቢን ለማሻሻልና ቁልፍ ተቋማትን ለማጠናከር ትልልቅ እርምጃዎችን መውሰዷን ጠቁመዋል። በተጨማሪም የዓለም የንግድ ድርጅትን ለመቀላቀል ሰፋፊ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ጠቅሰው ይህም ግልጽነትንና በሕግና በደንብ የተመራ የንግድ ሥርዓትን ያጠናክራል ብለዋል። እንዲሁም ቀጣናውን የሚያስተሳስሩ ስትራቴጂካዊ የትራንስፖርትና የሎጂስቲክስ ኮሪደሮች ላይ ኢንቨስት እያደረገች መሆኑን ገልጸዋል። ይህም ከቀጣናዊ ቃል ኪዳኖች ጋር የሚጣጣሙና እርስ በርስ የሚያጠናክሩ ማሻሻያዎችን ለማስፈጸም ያለንን ቁርጠኝነት ያሳያሉ ብለዋል። የስብሰባው ተሳታፊዎች ግልጽ፣ ወደፊትን ያማከለና በዜጎች ዕለታዊ ሕይወት ውስጥ ወደ ተጨባጭ እውነታ የሚቀይሩ ተግባራዊ እርምጃዎች ላይ እንዲተኮርም ጥሪ አቅርበዋል።
የፖሊሲ ማሻሻያ መደረጉና የተቀላጠፈ አገልግሎት መሰጠቱ ለኢንዱስትሪ ዘርፉ እመርታ የላቀ አስተዋጽኦ አበርክተዋል
Sep 3, 2026 109
ወላይታ ሶዶ፤ ነሐሴ 28/2018(ኢዜአ)፦ የመንግሥት የፖሊሲ ማሻሻያዎችና የተቀላጠፉ አገልግሎቶች መሰጠት መጀመሩ ለኢንዱስትሪ ዘርፉ እመርታ የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ምሁራን ገለጹ። የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የኢንዱስትሪ ዘርፉን ማነቆዎች በመፍታት የተሻለ እድገትና ማንሰራራት እንዲመጣ ማድረጉ ይታወቃል። በተለይም የውጭ ምንዛሬ አቅርቦትን በማሻሻል፣ በሀገር ውስጥ የሚመረቱ ተኪ ምርቶች እንዲበራከቱ፣ የወጪ ንግድ ተወዳዳሪነትን በማሳደግ የላቀ አስተዋጽኦ አበርክቷል። ከዚህ በተጨማሪ ግልጽና ገበያ መር የሆነ የፋይናንስና የውጭ ምንዛሬ ስርዓት በመዘርጋቱ የውጭ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ ዘርፎች ኢንቨስት ማድረግ እንዲችሉ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል። በተለይም በማኑፋክቸሪንግና በኢንዱስትሪ ፓርኮች ላይ የውጭና የሀገር ውስጥ ባለሃብቶች ተሳትፎ በእጅጉ እያደገ መምጣት ችሏል። በመሆኑም በመንግስት የተወሰዱ የፖሊሲ ማሻሻያዎችና የተቀላጠፉ አገልግሎቶች በኢንዱስትሪ ዘርፉ ትልቅ እመርታ እንዲመዘገብ ያስቻሉ መሆኑን ኢዜአ ያነጋገራቸው የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገልጸዋል። የዩኒቨርሲቲው ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዘርፍ ምክትል ዲን ኢንጂነር መንግስቱ መና፤ የመንግስት የፖሊሲ ማሻሻያዎችና የተቀላጠፉ አገልግሎቶች ለኢንዱስትሪ ዘርፉ እመርታ የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን አስረድተዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኮችን የማምረት አቅም በማሳደግ የውጭ ምንዛሬን ከማዳን በተጨማሪ ተኪ ምርቶችን በማምረት ለኢኮኖሚው መነቃቃትና ለበርካታ ዜጎችም የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉን አንስተዋል። በዩኒቨርሲቲው የኢንዱስትሪያል አስተዳደርና ኢንጂነሪንግ ኢኮኖሚክስ መምህርና ተመራማሪ ጌታሁን ሶርሳ፤ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኢንዱስትሪ ዘርፍ እየተመዘገበ ያለው ስኬት አበረታች ስለመሆኑ ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ መስፋፋት ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በብዛትና በጥራት በማምረት የነበረውን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ወጪ መቀነስ ያስቻለ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ዘርፉ የውጭ ምንዛሪን ማዳንና ሀገራዊ የምግብ ዋስትናን በአስተማማኝ ሁኔታ ለማረጋገጥ እያገዘ በመሆኑ እነዚህን መልካም ጅምሮች ማስቀጠል ይገባል ብለዋል።
በኦሮሚያ ክልል ከመኸር ሰብል የተሻለ ምርት ለማግኘት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ
Sep 3, 2026 135
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ከ2018/19 የመኸር ሰብል የሚጠበቀውን ምርት ለማግኘት የሚያስችሉ የሰብል እንክብካቤ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በተያዘው የምርት ወቅት የታቀደውን የምርት መጠን ለማሳካት የእርሻ መሬትን በአግባቡ አዘጋጅቶና ግብአቶችን ተጠቅሞ በዘር ከመሸፈን በመቀጠል ሰብሉን ከአረም፣ ከነፍሳትና ከተለያዩ በሽታዎች መከላከል ወሳኝ ነው። የክልሉ ግብርና ቢሮ ከዚህ አኳያ አርሶ አደሩን ዘመናዊና ባህላዊ የሰብል ጥበቃ ዘዴዎችን አቀናጅቶ እንዲጠቀም ባለሙያዎችን መድቦ ድጋፍ በማድረግ ላይ ይገኛል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ ከመኸር አዝመራ የተሻለ ምርት በመሰብሰብ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ ከፍተኛ ርብርብ እየተደረገ ይገኛል። በክልሉ በምርት ዘመኑ ከ11 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬትን በተለያዩ ሰብሎች በማልማት ከ380 ሚሊዮን 6 መቶ ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል። ከዚህ ውስጥም እስካሁን 9 ሚሊዮን 627 ሺህ 749 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች መሸፈኑን ገልጸዋል። ምርታማነትን ለመጨመር የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማሳደግ መቻሉን የጠቆሙት ኃላፊው፤ በዚህም 5 ሚሊዮን 158 ሺህ 516 ሄክታር የሚሆነው መሬት በትራክተር መታረሱን አስረድተዋል። ከግብዓት አቅርቦት አንጻርም ከቀረበው ከ10 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ እስካሁን ከ7 ሚሊዮን 677 ሺህ ኩንታል በላይ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን አስታውቀዋል። አቶ ጌቱ እንደተናገሩት የታቀደውን ምርት ለማሳካት በተለይም የተቀናጀ የሰብል እንክብካቤና ጥበቃ ሥራ በትኩረት እየተከናወነ ይገኛል። አርሶ አደሩ ማሳቸውን በየጊዜው በመከታተልና በመፈተሽ የበሽታና የአረም ቁጥጥር ሥራዎችን በልዩ ትኩረት እያከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል። እንዲሁም አርሶ አደሩ በደቦ ባህላዊ የመረዳዳት ስልት በመጠቀም የኩትኳቶና አረም የመንቀል ተግባርን በሰፊው እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የሰብል እንክብካቤና ጥበቃ ስራውን ለማጠናከርም የአረም እና ተባይ ማጥፊያ ኬሚካሎች ለአርሶ አደሩ እንዲሰራጩ መደረጉን ኃላፊው ገልጸዋል። በዚህም በተቀናጀና በተናበበ አሰራር በተከናወኑ ስራዎች በአሁኑ ወቅት የሰብሉ ቁመና በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ፈጣን፣ ጠንካራ እና ሁሉንም ያካተተ ኢኮኖሚ መገንባቷን ትቀጥላለች - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 3, 2026 149
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ፈጣን፣ ጠንካራ እና ሁሉንም ያካተተ ኢኮኖሚ መገንባቷን ትቀጥላለች ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። በሀገራችን የመጀመሪያውን የተለየ የቤት መግዣ ብድር መልሶ ማጠናከሪያ ኩባንያ ለማቋቋም የሚያስችለውን ታሪካዊ የትብብር ማዕቀፍ፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እና በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን (IFC) መካከል ስምምነት ዛሬ አከናውነናል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልእክት በ100 ቢሊዮን የኢትዮጵያ ብር ካፒታል የተቋቋመው እና በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን ደግሞ 200 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ አስተዋፅኦ የሚያደርግበት ተቋም መሆኑን ገልጸዋል። በባንክ ዘርፋችን ውስጥ የጥሬ ገንዘብ ፍሰት አለመመጣጠንን የሚቀርፍ እና በመላው ኢትዮጵያ ተደራሽ የሚሆን የቤት መግዣ ብድር ፋይናንስን የሚያስገኝ ይሆናልም ብለዋል። ይህ አጋርነት በተመጣጣኝ ዋጋ የሚገነቡና የኢትዮጵያውያንን ክብር የጠበቁ 1.5 ሚሊዮን ቤቶችን ለማቅረብ እንዲሁም በፋይናንስ ሥርዓታችን ውስጥ የግል ዘርፉን ተሳትፎ ለማስፋት ያስቀመጥነውን ግብ የሚያሳካ ወሳኝ እርምጃ ነው ሲሉም ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልእክትም ኢትዮጵያ ፈጣን፣ ጠንካራ እና ሁሉንም ያካተተ ኢኮኖሚ መገንባቷን ትቀጥላለች ብለዋል።
የመደመር እሳቤ ለኢኮኖሚ ትንሣኤ፡የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ፍሬዎች
Sep 3, 2026 97
ሀገራችን በማካሄድ ላይ ያለችው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ሁሉን አቀፍ፣ ዘርፈ ብዙና አካታች ነው፡፡በአግባቡ ከተተገበረ መሠረታዊና ዘላቂ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጥቅም ያስገኛል።ይህም እውን የሚሆነው በአንዴ ሳይሆን በሂደት ነው፡፡የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በኢኮኖሚው ውስጥ የሚታየውን ማክሮ ኢኮኖሚያዊ መዛባት ለማስተካከል፣ የሕዝቡን የኑሮ ሁኔታ ለማሻሻል፣ የኢኮኖሚውን ቀጣይ ዕድገት ለማረጋገጥ፣ ሀገሪቱ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት በተሻለ መልኩ እንድትጠቀም ለማድረግ፣ከዓለም ኢኮኖሚ ጋር ያለንን ግንኙነትና ተወዳዳሪነት ለማጎልበት፣ የሥራ ዕድልን ለማስፋት፣ ቁጠባና ኢንቨስትመንትን ለማበረታታት፣ በጥቅሉ ሁሉም ዜጋ ተጠቃሚ የሚሆንበትን የብልጽግና ትሩፋት ለማሳደግ የሚኖረው ፋይዳ የጎላ ነው። ከማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የተነሣ በሚቀጥሉት ዓመታት የኢኮኖሚው ዕድገት ተጠናክሮ ይቀጥላል፤ ምርትና ምርታማነት ያድጋል፤ የዋጋ ግሽበት ወደ ነጠላ አሐዝ ይወርዳል፤ የመንግሥትን ገቢ የማሳደግና ለልማት የሚውል ሀብት በዋናነት ከሀገር ውስጥ ምንጮች የማሰባሰብ አቅም ይጎለብታል፤ የወጪ ንግድ ይስፋፋል፤ የውጭ ሐዋላ ፍሰት ያድጋል፤ የሀገር ውስጥም ሆነ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ይጨምራል፤ የሥራ ዕድል ይስፋፋል፤ ከኢኮኖሚው ዕድገት፣ ከብሔራዊ ባንክ የቁጥጥርና የሱፐርቪዥን አቅም መጎልበት እንዲሁም ከቴክኖሎጂ መስፋፋትና ከውጭ ባንኮች የመግባት ዕድል ጋር ተያይዞ የፋይናንስ ዘርፉ ጤናማነት፣ ዕድገትና ተወዳዳሪነት ይጠናከራል፡፡ በጥቅሉ፣ ሀገሪቱ በአካባቢዋም ሆነ ከሰሐራ በታች ካሉ ግዙፍ ኢኮኖሚዎች መካከል በቀዳሚነት እንደምትቆም ይጠበቃል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ፋይዳው የጎላ እንደሚሆን ከላይ የተገለጸ ቢሆንም፣ አንዳንድ አሉታዊ ጫናዎችን እንደሚያስከትል ታሳቢ ተደርጓል።በመሆኑም፣ መንግሥት በተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ላይ ሊደርስ የሚችለውን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጫና ለማርገብ የሚረዱ በመሠረታዊ ሸቀጦች ላይ ያለውን ድጎማ በጊዜያዊነት ለመቀጠል፣ የመንግሥት ሠራተኞችን ደሞዝ ለማሻሻልና በከተማም ሆነ በገጠር የሴፍቲኔት መርሐ ግብርን አጠናክሮ ለማስኬድ በገባው ቃል መሠረት በየደረጃው ተፈጻሚ በማድረግ ላይ ይገኛል። ከዚህ ሌላ፣ ጊዜያዊ ወጪዎችንና የውጭ ምንዛሪ ማሻሻያ የሚያስከትላቸውን ጫናዎች ለመቀነስ የሚረዳ 14 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ትልቅ የገንዘብ ድጋፍ ከውጭ አጋሮች እንደሚገኝ ቃል ተገብቷል፡፡ ይህ ዓለም አቀፍ አጋሮች በሚቀጥሉት ዓመታት ለኢትዮጵያ ለመስጠት ያቀዱት ትልቁ የተቀናጀ የገንዘብ ርዳታ ነው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክም የዋጋና የውጭ ኢኮኖሚ የማረጋጋት፣ የፋይናንስ ዘርፍ ጤናማነትና ዕድገት የማረጋገጥ ቁልፍ ሚናዎቹን ለመወጣት የሚያስችል በቂ ዝግጅት አድርጎ ወደ ሥራ ገብቷል፡፡ በተለይም፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ የዋጋ ንረትን የሚያረግብባቸውን አዳዲስ የገንዘብ ፖሊሲ መሣሪያዎች ሥራ ላይ ማዋል ጀምሯል። የገንዘብ ሚኒስቴር በበኩሉ ጠንካራ የገቢ መሠረት ለመጣልና የዋጋ ንረትን የሚያባብሱ (ለምሳሌ፣ ከብሔራዊ ባንክ ቀጥታ ብድር መውሰድን የመሳሰሉ) የመበደሪያ ስልቶችን ሳይጠቀም የመንግሥት ወጪን ለማሳደግ የሚያስችሉ ርምጃዎችን እየተገበረ ይገኛል፡፡
ብራዚል ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የንግድ ትስስር ለማስፋት የሚያስችላትን ቋሚ ጽሕፈት ቤት በአዲስ አበባ ከፈተች
Sep 2, 2026 361
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 27/2018(ኢዜአ) ፦ በኢትዮጵያ እና በብራዚል መካከል ያለውን የኢኮኖሚ፣ የንግድ እና የኢንቨስትመንት ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር የብራዚል ንግድ እና ኢንቨስትመንት ማስተዋወቂያ ኤጀንሲ (አፔክስብራዚል) ቋሚ ጽሕፈት ቤቱን በአዲስ አበባ ከፍቷል። በመክፈቻው መርሃ ግብር ከፍተኛ የኢትዮጵያ እና የብራዚል የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የንግድ ማህበረሰብ ተወካዮችና ዲፕሎማቶች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን(ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ ቋሚ ጽህፈት ቤቱ በአዲስ አበባ መክፈቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ተጨባጭ ስትራቴጂካዊ ቅንጅት መጀመሩን የሚያበስር መሆኑን ገልፀዋል። አፔክስብራዚል ለኢንቨስተሮች የመረጃ እጥረቶችን በማስወገድ፣ አካባቢያዊ የገበያ መረጃ በመስጠት እና የንግድ ትስስርን በማጠናከር ረገድ ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የብራዚልን የላቀ በቴክኖሎጂ የተደገፈ የግብርና ልምድ ከኢትዮጵያ ሰፊና ለም መሬት ጋር በማጣመር በቡና፣ በምርጥ ዘር ፣ በእንስሳት ሀብት እና ዘመናዊ አግሮ-ቢዝነስ ላይ መስራት ያስችለዋል ሲሉ ገልፀዋል። ኮሚሽኑ ወደ ኢትዮጵያ ገበያ ለሚገቡ የብራዚል ኩባንያዎች አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግም አረጋግጠዋል። በኢትዮጵያ የብራዚል አምባሳደር ክዣንዲር ፈሬራ ዶስ ሳንቶስ እንደተናገሩት፤ አፔክስብራዚል በአዲስ አበባ ቋሚ ጽሕፈት ቤት መክፈቱ በሁለቱ ሀገራት የኢኮኖሚ ግንኙነት ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው። በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው የሁለትዮሽ ግንኙነት ማደጉን የሚያሳይ እና ወደፊት ለመድረስ ያለውን ታላቅ ምኞት የሚያንጸባርቅም ነው ብለዋል። ጽሕፈት ቤቱ የብራዚል ኩባንያዎች የኢትዮጵያን ገበያ አማራጮችን እንዲገነዘቡ፣ አጋሮችን እንዲያገኙ እና የገበያ መረጃዎችን እንዲያገኙ የሚያስችል እንደሆነ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ባለሀብቶችም በዓለም ትልልቅ ኢኮኖሚዎች በአንዱ በሆነችው ብራዚል ውስጥ ያሉ እድሎችን እንዲጠቀሙ ይረዳቸዋል ብለዋል። አዲስ አበባ የአፍሪካ ዲፕሎማሲያዊ መዲና በመሆኗ አፔክስብራዚል ከኢትዮጵያ ባለፈ በምስራቅ አፍሪካ እና በሰፊው የአፍሪካ ገበያ እንደ ግብርና፣ አቪዬሽን፣ መድኃኒት ማምረት፣ መሠረተ ልማት እና ታዳሽ ኃይል ባሉ ዘርፎች ያሉ እድሎችን እንድትጠቀም ያደርጋታል ሲሉ ገልፀዋል። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአውሮፓ እና አሜሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር መለስ ዓለም (ዶ/ር) በበኩላቸው አፔክስብራዚል በአዲስ አበባ ቋሚ ጽሕፈት ቤት መክፈቱ በኢትዮጵያ እና በብራዚል መካከል ባለው የኢኮኖሚ አጋርነት ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው ብለዋል። የአፔክስ ጽሕፈት ቤት የንግድ እና ኢንቨስትመንት ትስስርን የበለጠ ለማሳደግ፣ የንግድ አጋርነትን ለማመቻቸት እና በኢትዮጵያ እና በብራዚል ባለሀብቶች መካከል ትርጉም ያለው እና ተጨባጭ ትስስርን ለማስፋፋት የሚያገለግል መድረክ እንደሚሆንም ተናግረዋል።
ከምስራቅ ቦረና ዞን ቆላማ ወረዳዎች ከዘንድሮ የበልግ አዝመራ ከ2 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቧል
Sep 2, 2026 115
ነገሌ ቦረና፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ቦረና ዞን ከዘንድሮው የበልግ አዝመራ ከ2 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በምስራቅ ቦረና ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት የአዝርእት ልማትና ጥበቃ ባለሙያ አቶ ቦነያ ሁቃ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ከ176 ሺህ 20 ሄክታር በላይ መሬት በበልግ አዝመራው በተለያዩ ሰብሎች መልማቱን አስታውሰዋል፡፡ በልማቱ ከተሳተፉት 143 ሺህ 288 ከፊል አርብቶ አደሮች መካከል 23 ሺህ 614 ሴቶች እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡ በዞኑ ቆላማ ወረዳዎች ከለማው ከዚሁ መሬት 2 ሚሊዮን 126 ሺህ ኩንታል የሚጠጋ አጠቃላይ ምርት መሰብሰቡን አስታውቀዋል፡፡ በዞኑ የበልግ አዝመራ ከተመረቱት የሰብል አይነቶች መካከል ስንዴ፣ ጤፍ፣ በቆሎ፣ ቦለቄ፣ ማሽላና ሰሊጥ ዋና ዋናዎቹ እንደሆኑ ጠቁመዋል፡፡ ዘንድሮ ከዞኑ ሁሉም ወረዳዎች ከበልግ አዝመራ የተሰበሰበው አጠቃላይ ምርት ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር ብልጫ ያለው ነው ብለዋል፡፡ በበልግ አዝመራው ልማት ከተሳተፉት የዞኑ ነዋሪዎች መካከል የነገሌ ቦረና ከተማ ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ አቶ አበራ ሞገስ ከበልግ አዝመራ ካለፉት አመታት ሁሉ የተሻለ ምርት መሰብሰባቸውን ገልጸዋል፡፡ የተሻሻለ የግብርና አሰራር፣ የምርት ማሳደጊያ አጠቃቀምና የተስተካከለ የዝናብ ስርጭት መኖሩ ውጤት ማስገኘቱን ጠቅሰዋል፡፡ የኩታ ገጠም አስተራረስ፣ በመስመር መዝራትና ሜካናይዜሽን አጠቃቀም ከተሻሸሉ የግብርና አሰራሮች መካከል ዋና ዋናዎቹ እንደሆኑም ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ በምስራቅ ቦረና ዞን ከመጋቢት አጋማሽ እስከ ሚያዝያ ወር የዝናብና የዘር፣ ከሐምሌ እስከ ነሔሴ ወር ደግሞ የምርት መሰብሰቢያ ወቅት እንደሆነ ይታወቃል፡፡
የከተማ ግብርና ዘርፍ የገቢ አቅማችንን ለማሳደግ አግዞናል- በሸገር ከተማ በዘርፉ የተሰማሩ
Sep 2, 2026 108
ሱሉልታ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፡- በከተማ ግብርና በመሰማራታቸው የገቢ አቅማቸው ማደጉን በሸገር ከተማ በዘርፉ የተሰማሩ አርሶአደሮች ተናገሩ፡፡ የሸገር ከተማ አርሶ አደሮች ቀን «ዘመናዊ ገበሬና ዘመናዊ ግብርና ለአጠቃላይ ብልፅግና» በሚል መሪ ቃል በከተማው ሱሉልታ ክፍለ ከተማ በተለያዩ ሥነ-ሥርዓቶች እየተከበረ ይገኛል። አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግም የባዛር እና ኤግዚቢሽን ፕሮግራም የተዘጋጀ ሲሆን፣ የግብርና ምርቶች፣ ማሽነሪዎች፣ የምርት ማሳደጊያ ግብዓቶችና ሌሎችም በበዛሩና ኤግዚቢሽኑ ላይ ለእይታና ሽያጭ ቀርበዋል። የአርሶ አደሮቹ ቀን አከባበር ዋነኛ ዓላማም በከተሞች በከተማ ግብርና ዘርፍ በስፋት በመሰማራት በምግብ ራስን ከመቻል ባሻገር፣ ትኩስ የግብርና ምርቶችን በበቂ መጠንና በፍትሐዊ ዋጋ ለገበያ በማቅረብ የኑሮ ውድነትን መቀነስ እና ገበያውን ማረጋጋት እንደሆነም ተገልጿል። የመርሃ ግብሩ ተሳታፊ አርሶ አደሮች ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፣ አስተዳደሩ የከተማ ግብርናን በማስፋፋትና ዘመናዊና ዘላቂነት ያለው የምግብ ዋስትና ማረጋገጫ ስራዎችን በማከናወን ረገድ እየደገፋቸው እንደሚገኝ ገልጸዋል። አርሶ አደሮቹ የመንግስትን ድጋፍ መነሻ በማድረግ ምርታማነታቸውን ማሳደጋቸውን ጠቅሰው፣ የተፈጠረላቸውን የገበያ ዕድል በመጠቀምም የግብርና ምርቶቻቸውን በማቅረብ ላይ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። በተለይም በእንስሳት እርባታ ላይ በመሰማራት ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን የገለፁት አርሶ አደሮቹ፣ የእንስሳት እርባታን በማዘመን ረገድ ትልቅ ስራ እየሰሩ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል በንብ እርባታና ማር ምርት ላይ የተሰማሩት አቶ አበራ ሰቦቃ እንደተናገሩት፣ እየሰሩት ባለው ስራ ተጠቃሚነታቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ምርታቸውን ለገበያ በማቅረብ ገቢያቸውን እያሳደጉ ነው። ወደፊትም ሀገር ውስጥ ገበያ ብቻ ከማቅረብ ሳይወሰን ወደ ውጭ የሚላከውን ምርት በማሳደግ ረገድ ድርሻችንን እንወጣለን ብለዋል። በተመሳሳይ ወይዘሮ አሰገደች ስሜ በእንስሳት ተዋጽኦ አቅርቦት ላይ በማህበር ተደራጅተው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በተፈጠረው የገበያ ትስስር ተጠቃሚ መሆናቸውን የጠቆሙት አርሶ አደሯ፤ ከባለሙያዎችና ከመንግስት ጋር በቅንጅት እየሰሩ እንደሚገኙና በቀጣይም ስራቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። የሸገር ከተማ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ደጃኔ በቀለ በበኩላቸው፤ ከተማዋ ቀደም ሲል ምርት ሳታመርት ከውጭ የምትገዛ እንደነበረች አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ግን በዘመናዊ ግብርና በማምረት ለገበያ ማቅረብ መጀመሯን ገልጸዋል። በከተማ ደረጃ ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ በመፍጠርና ከቴክኖሎጂ ጋር ከማስተዋወቅ አንጻር በተከናወኑት ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል።
በጋምቤላ ክልል የእንስሳት ጤና አጠባበቅና ዝርያን በማሻሻል ምርታማነትን የማሳደግ ተግባር ውጤት አስገኝቷል
Sep 2, 2026 137
ጋምቤላ፣ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፡-በጋምቤላ ክልል የእንስሳት ጤናን በመጠበቅና ዝርያን በማሻሻል ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት ማስገኘታቸውን የክልሉ ዓሣና እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ25 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሊትር በላይ የወተት ምርት መገኘቱን ቢሮው ገልጿል። የክልሉ እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ክርሚስ ሌሮ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በጋምቤላ ክልል ያለውን የእንስሳት ሀብት ምርታማነት ለማሳደግ የተሻሻሉ ዝርያዎችን የማስራጨትና የእንስሳት ጤና ላይ እየተሰራ ነው። ይህም ውጤት ማስገኘቱን ገልጸው፣ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የእንስሳት ሀብት ልማቱን ከሌማት ቱሩፋት መርሃ ግብር ጋር በማስተሳሰር የተሰራው ሥራም ለውጤቱ አስተዋጾ ማድረጉን ተናግረዋል። ለእዚህም በ2018 በጀት ዓመት 25 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሊትር ወተት፣ ከ12 ሚሊዮን በላይ እንቁላል እና ሌሎች የእንስሳት ተዋጾ ምርት መገኘቱን ጠቅሰዋል። ቢሮው የእንስሳትን ጤና ለማስጠበቅም ዘመናዊ ላቦራቶሪ የማደራጀትና የእንስሳት ጤና ኬላዎችን ተደራሽ የማድረግ ሥራ መሰራቱን ገልጸዋል። በተለይም በማጃንግ ዞን ጎደሬ ወረዳ በሰው ሰራሽ ማዳቀል የተጀመሩትን የወተት ላሞች ዝርያ የማሻሻል ሥራዎች በአዲሱ በጀት ዓመትም ወደ ሌሎች ወረዳዎች የማስፋት እንቅስቃሴ መጀመሩን ተናግረዋል። የተሻሻሉ የእንቁላልና የሥጋ ዶሮዎችን በዘርፉ ልማት ለተሰማሩ አርቢዎች ተደራሽ በማድረግ ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው ብለዋል። የእንስሳት ሀብት ልማቱን ከሌማት ቱሩፋት ኢንሼቲቩ ጋር ማስተሳሰር ከተጀመረ ወዲህ የባለሃብቱ፣ የአርሶ እና የአርብቶ አደሩ የዘርፉ ተጠቃሚነት ማደጉን ጠቅሰዋል። ይህም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ከማሳደጉ ባለፈ በከተሞች የዋጋ ንረትን ለማርገብ እያገዘ መሆኑን ጠቁመዋል። በክልሉ ማጃንግ ዞን ጎዴሬ ወረዳ በተሻሻሉ የወተት ላሞች እርባታ ሥራ የተሰማረው አቶ ቢተውልኝ ግርማ እንዳሉት የተሻሻሉ የወተት ላሞችን በማርባት ወተትና የወተት ተዋጾን ለገበያ በማቅረብ ገቢያቸውን እያሳደጉ ናቸው። በአሁኑ ወቅት ሥራውን በማስፋት በቀን ከ60 ሊትር በላይ ወተት ለህብረተሰቡ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። በዶሮ እርባታ ሥራ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የክንድዬና ጓድኞቹ የዶሮ እርባታ ማህበር ተወካይ አቶ ክንድዬ ጥጋቡ ናቸው። ማህበሩ የእንቁላልና የሥጋ ደሮዎችን በማርባት በጋምቤላ ከተማና አካባቢው ላሉ ነዋሪዎች በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረበ መሆኑን ገልጸዋል።
የመስኖና የሜካናይዜሽን ሽግግር በኢትዮጵያ ግብርና ዘርፍ ከተመዘገቡት ስኬቶች ዋነኞቹ ናቸው-ምሁራን
Sep 2, 2026 82
ጅማ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ):- ከዝናብ ጥገኝነት በመላቀቅ ወደ መስኖ ልማትና ሜካናይዜሽን እየተደረገ ያለው ሽግግር፣ በኢትዮጵያ ግብርና ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የከፈተ ታሪካዊ እርምጃ መሆኑን ምሁራን አስታወቁ። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዋና መደገፊያ የሆነው የግብርናው ዘርፍ፣ ለዘመናት በባህላዊ ማረሻና በዝናብ ውኃ ላይ ብቻ ጥገኛ ሆኖ መቆየቱ የሚታወቅ ነው። ይህ ሁኔታ አገሪቱን ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖና ለምግብ ዋስትና እጦት ተጋላጭ አድርጓት ቆይቷል። ይሁን እንጂ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በስፋት እየተተገበሩ ያሉ የስንዴ መስኖ ልማት፣ የበጋ መስኖ አመራረት እና የግብርና መሣሪያዎች ሜካናይዜሽን የዘርፉን ምርታማነት በከፍተኛ ደረጃ እየቀየሩት ነው። በዚህ ጉዳይ ላይ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የጅማ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን፤ ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት ግብርናውን ከባህላዊ አሰራር በማላቀቅ ወደ መስኖ ልማት፣ ሜካናይዜሽንና ዘመናዊ አመራረት ለማሸጋገር ሰፊ የፖሊሲና የትግበራ ስትራቴጂዎችን በማካሄድ ላይ ትገኛለች ብለዋል። በዩኒቨርሲቲው የግብርናና እንስሳት ሕክምና ኮሌጅ የእንስሳት ሥነ-ምግብ መምህርና ተመራማሪ ዋሲሁን ሀሰን (ዶ/ር) በግብርናው ዘርፍ የታዩ ለውጦች ከምርት መጠን በላይ የአመራረት ሥርዓቱን የሚቀይሩ መሆናቸውን አስረድተዋል። በተለይም የመስኖ ልማት መስፋፋቱ ግብርናው ከዝናብ ጥገኝነት እንዲላቀቅ ያስቻለ ሲሆን፣ ይህም የምርት ወቅትን በማስፋት በዓመት በተለያዩ ወቅቶች ምርት ለማምረት ዕድል መፍጠሩን ጠቁመዋል። ሌላው የግብርናው ዘርፍ ለውጥ ማሳያ የሆነው ሜካናይዜሽን መስፋፋቱ መሆኑን ምሁሩ አመልክተዋል። በዚህም ከባህላዊ የማረሻ ዘዴዎች በመሻገር ትራክተሮችንና ሌሎች የግብርና ማሽነሪዎችን በመጠቀም የማረስ፣ የማጨድና የመውቃት ሥራዎችን በሜካናይዜሽን ለማከናወን የተደረገው ጥረት በግብርናው ላይ እየታየ ላለው ፈጣን ለውጥ አንዱ ማሳያ መሆኑን አስረድተዋል። ይህም በሰው ጉልበት የሚወስደውን ጊዜ እና የምርት ብክነትን በመቀነስ ምርትን በጥራትና በብዛት ለማሳደግ አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ነው የጠቀሱት። በተጨማሪም የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት መስፋፋቱ ኢትዮጵያ ከራሷ የስንዴ ፍላጎት አልፋ ወደ ውጭ ገበያ ለመላክ ያስቻላት ዋና የግብርና ለውጥ መሆኑን አስረድተዋል። የሌማት ትሩፋት እንቅስቃሴም በጓሮ እርሻ፣ በዶሮ እርባታና በንብ ማነብ የተሠሩ ሥራዎች የቤተሰብ የምግብ ስርዓትን ከማሳደግ ባለፈ ተጨማሪ ገቢ ለማመንጨት ዕድል መፍጠሩን የተናገሩት ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የግብርና እና ዕንስሳት ህክምና ኮሌጅ ዲን እና የአፈር ልማት፣ የሰብል እንክብካቤና ንጥረ-ነገር ባለሙያ ሰለሞን ቱሉ (ዶ/ር) ናቸው። በዚህም የወተትና የእንቁላል ምርት መጨመሩን ጠቁመው፣ በገጠርና በከተማ የሚገኘው ማኅበረሰብ በእነዚህ የግብርና ሥራዎች ላይ በስፋት እንዲሳተፍ መደረጉን ገልጸዋል። ከእህል ምርት ባሻገር በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ላይ የተሠሩ ሥራዎችም ለኢትዮጵያ የውጭ ምንዛሬ ገቢ መጨመር አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን እንደ አብነት አስረድተዋል። በተለይም የአቮካዶ ምርት መስፋፋትና የቡና ምርት ኤክስፖርት ከፍተኛ ገቢ ማስገኘታቸው በዘርፉ ከታዩ ዋና ዋና ለውጦች መካከል መሆኑን ጠቁመዋል። ከምርቱ ማደግና መስፋፋት በተጨማሪ ግብርናው ባለፉት አመታት ለበርካቶች የስራ ዕድል የተፈጠረበት ነው ብለዋል። በየአካባቢው በኩታ ገጠም ተደራጅተው የሚያመርቱ ወጣቶች እና አርሶ አደሮች ከራሳቸው አልፈው ለዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል የፈጠሩበት መሆኑን አስረድተዋል። በአጠቃላይ እነዚህ ለውጦች የኢትዮጵያን ግብርና ከዝናብ ጥገኝነትና ከባህላዊ አሰራር በማሻገር ወደ መስኖ፣ ሜካናይዜሽንና ዘመናዊ አመራረት እያሸጋገሩት ያሉ ዋና ማሳያዎች መሆናቸውን ምሁራኑ ገልጸዋል። ይህም የምግብ አቅርቦትን ከማሻሻል ባለፈ የገቢ ምንጭን፣ የሥራ ዕድልንና የውጭ ምንዛሬን ለማሳደግ እያበረከተ ያለውን ሚና ያሳያል ብለዋል።
በክልሉ ኢንዱስትሪዎችን በማስፋፋት ተኪ ምርቶችን የማምረት ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል -ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን
Sep 2, 2026 158
አሶሳ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፡- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ኢንዱስትሪዎችን በማስፋፋት ተኪ ምርቶችን የማምረት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ በአሶሳ ከተማ በግል ባለሃብት የተገነባውን የአሶሳ ዱቄት ፋብሪካ መርቀው ስራ አስጀምረዋል። ፋብሪካው በ120 ሚሊየን ብር የተገነባ ሲሆን ለ40 ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠሩ ተመላክቷል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን በወቅቱ እንደገለፁት፤ ክልሉ ለኢንቨስትመንት ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ኢንዱስትሪዎችን የማስፋፋትና እሴት የተጨመረባቸውን የፋብሪካ ውጤቶች እንዲያመርቱ እየተደረገ ነው ። የኢንዱስትሪዎች መስፋፋትም ከውጪ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካት እየተቻለ መሆኑን ጠቁመው ይህም የውጪ ምንዛሬን ወጪን ለማስቀረት እና በቂ ምርቶችን ለህብረተሰቡ ለማድረስ የሚያግዝ መሆኑን አመልክተዋል። ክልሉ ለኢንዱስትሪዎች መስፋፋት ትልቅ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን ጠቅሰው፤ በዘርፉ ለሚሰማሩ ባለሃብቶች አስፈላውን ድጋፍ በማድረግ ተግባሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል ። የአሶሳ ዱቄት ፋብሪካ በከተማው ለሚገኙ የዳቦ ፋብሪካዎች ምርቱን በማቅረብ ከሌላ ቦታ የሚመጣን የዱቄት ወጪ ለመቀንስና ፍላጎትና አቅርቦትን ለማስተካከል አቅም የሚፈጥር መሆኑን አመልክተዋል ። የክልሉ ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ አመንቴ ገሺ በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ 71 አነስተኛ፣ መካከለኛ እና ትልልቅ ኢንዱስትሪዎች ተቋቁመው ወደሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። አሶሳ ዱቄት ፋብሪካ በክልሉ በቅርቡ ወደሥራ ከገቡ ዘጠኝ ትልልቅ ኢንዱስትሪዎች መካከል አንዱ መሆኑን አቶ አመንቴ አንስተዋል። የአሶሳ ዱቄት ፋብሪካ ባለቤት እና ሥራ አስኪያጅ ዮሐንስ ወንዳፈራው፤ ፋብሪካው በቀን 420 ኩንታል ዱቄት የማምረት አቅም እንዳለው ገልጸው፤ ከስንዴ ዱቄት ባሻገር በቀጣይ የቦቆሎ ዱቄትን ጨምሮ የተለያዩ ምርቶችን ለማቅረብ ማቀዱን አብራርተዋል። ለፋብሪካው ግብዓት የሚሆን ምርት ለማምረት የሚያስችል የእርሻ ማሳ አዘጋጅቶ ወደ ስራ ለመግባት በሂደት ላይ መሆኑን ስራ አስኪያጁ ገልጸዋል። በተያያዘም የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን መርቀው የከፈቱ ሲሆን የግብርና፣ የኢንዱስትሪ እና የጨርቃጨርቅ ምርቶችና ውጤት ቀርበዋል።
የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ዘርፉን ለማሳለጥ ቅንጅታዊ አሰራሮችን አጠናክሮ መቀጠል ይገባል- ምክትል ርእሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ./ር)
Sep 2, 2026 100
ባህርዳር፤ ነሃሴ 27/2018 (ኢዜአ)፡- የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ዘርፉን ለማሳለጥ የሚያስችሉ ዘመናዊ አሰራሮችን በመከተል ቅንጅታዊ አሰራሮችን አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባ የአማራ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ./ር) ገለጹ። የአማራ ክልል መንገድ፣ ትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም እና የ2019 በጀት ዓመት የዕቅድ ትውውቅ መድረክ እያካሄደ ነው። በመድረኩ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)፤ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ አማራጮችን በማስፋትና በማሳለጥ ረገድ የተቀናጀ ጥረት ማድረግ እንደሚገባ ገልጸዋል። በአገልግሎቱ የሚስተዋሉ ክፍተቶችንና ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴዎችን ለመከላከል ጥብቅ ቁጥጥርና ዘመናዊ የአሠራር ሥርዓትን መከተል እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የምርት እንቅስቃሴ በአግባቡ እንዲሳለጥና ኢኮኖሚው ላይ እመርታዊ አስተዋጽኦ እንዲኖረው ሥራዎችን ማከናወን ተገቢ መሆኑን አንስተው፣ ለዚህም ቅንጅታዊ ጥረቱ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተናግረዋል። ለዚህም የክልሉ መንግሥት ለሦስቱም ዘርፎች በየዓመቱ ከፍተኛ በጀት በመመደብ በዘርፉ እመርታዊ ዕድገት ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል። በተለይ የመንገድ መሠረተ ልማትን በመገንባት ተደራሽነቱን ለማስፋት የተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤት የተመዘገበባቸው በመሆኑ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም መልካም ተሞክሮዎችን በማስፋትና ክፍተቶችን ለይቶ በማረም የመንገድ መሠረተ ልማት ትስስሩን ለማሳለጥ በትኩረት እንደሚሠራ አስገንዝበዋል። በትራንስፖርት ዘርፍም በአገልግሎት አሰጣጥ፣ ስምሪትና ሌሎች ተግባራት የሚስተዋለውን ውስንነት በመቅረፍ ሕዝቡ የተሳለጠ የትራንስፖርት አገልግሎት እንዲያገኝ ተሠርቷል ብለዋል። በተጨማሪም የሎጂስቲክስ አቅምን በማሳደግ በክልሉ የሚመረተውን ምርት ከብክነት በጸዳና በጥራት አከማችቶና አጓጉዞ ለገበያ ለማቅረብ የተጀመረው ተግባር ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተናግረዋል። ዘርፎቹ በአዲሱ በጀት ዓመትም በውጤታማነት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በየደረጃው የሚገኘው አመራር ተቀናጅቶና ተባብሮ ሊሠራ እንደሚገባ አሳስበዋል። የአማራ ክልል መንገድ፣ ትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ቢሮ ኃላፊ ጋሻው አወቀ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት አፈጻጸም የተሻለ ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን አብራርተዋል። ከዚህ ስኬት በመነሳትም በተያዘው በጀት ዓመት በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ የተሻለ እመርታ ለማስመዝገብ ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን አንስተዋል። የዚህ መድረክም ዋና ዓላማ የዘርፉን ስኬቶች ለማስቀጠል፣ ድክመቶችንና ጎደሎዎችን ለማስተካከል በሚያስችል መልኩ ለመገምገም መሆኑን ገልጸዋል። ለሌሎች ሴክተሮችም የዕድገት መሠረት የሆነውን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ዘርፍ በትብብርና ቅንጅት መምራት አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። በቴክኖሎጂ የተደገፈ የትራንስፖርት አገልግሎት ለተገልጋዩ ሕብረተሰብ ለመስጠት የሚያስችል አቅም መፈጠሩ ለቀጣይ ሥራ መሠረት ነው ብለዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለወጪ ንግድ ዘርፍ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር አዳዲስ የገበያ መዳረሻዎች በመክፈት አወንታዊ ሚና አለው
Sep 2, 2026 184
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለኢንቨስትመንትና ለወጪ ንግድ ዘርፎች ምቹ ሁኔታ በመፍጠር አዳዲስ የገበያ መዳረሻዎች በመክፈት አወንታዊ ሚና እየተጫወተ መሆኑን በዘርፉ የተሰማሩ ባለሃብቶችና የስራ ኃላፊዎች ገለፁ። በኢትዮጵያ የሆርቲካልቸር ልማት እና ኤክስፖርት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ፀጋዬ አበበ እንደገለጹት፤ በቀደሙት ዓመታት የነበሩ ቢሮክራሲዎች በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ደረጃ ተቀርፈዋል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት የኢኮኖሚ ሪፎርም በተካሄደበትና ምቹ የኢንቨስትመንት ሁኔታ በተፈጠረበት ወቅት ላይ በመሆናችን የሀገር ውስጥና የውጭ ባለሃብቶች በተመቻቸ ሁኔታ እንዲሰሩና ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። እንደ ቻይና፣ ህንድ እና የአውሮፓ ሀገራት ያሉ ኢንቨስተሮች በተጨማሪ እንደ ቬትናም ያሉ የሩቅ ምስራቅ ሀገራት ኢንቨስተሮች በተለያዩ ዘርፎች መዋዕለ ንዋያቸውን ለማፍሰስ እየመጡ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ይህም የተካሄደው የኢኮኖሚ ማሻሻያ ውጤት መሆኑን አብራርተዋል። በሌላ በኩል የቢኮ አግሮ ኢንዱስትሪ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ታምራት አዱኛ በበኩላቸው፤ ድርጅታቸው በዋናነት የስትሮበሪ ምርቶችን ለመካከለኛው ምስራቅ፣ ለሩቅ ምስራቅ፣ ለአፍሪካና ለአውሮፓ ሀገራት በመላክ ላይ እንደሚገኝ ገልፀዋል። መንግስት ከማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ጋር ተያይዞ አምርተው ለሚልኩ ድርጅቶች እያደረገ ያለው አበረታች ድጋፍ የበለጠ ለመስራት የሚያስችል ነው ብለዋል። በተለይም ከውጭ ምንዛሬ አቅርቦት፣ ከብድር ወረቀት አሰራርና ጋር ተያይዞ የባንክ አሰራሩ በጣም የተሳለጠ መሆኑን ተናግረዋል። ይህ አሰራር ድርጅታቸው እንደ ሲንጋፖርና ታይላንድ ካሉ የሩቅ ምስራቅ አገራት ጋር ያለውን የንግድ ግንኙነት በማጠናከር ወደ አዳዲስ ገበያዎች በቀላሉ እንዲገባ ትልቅ እድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል። የሻቫሞ ኤክስፖርት ኃ/የተ/የግ/ማህበር የኤክስፖርት ማናጀር አቶ ታሪኩ ጉተታ እንደተናገሩት፤ በቡና ኤክስፖርት ዘርፍ የአውሮፓ ገበያ በዋናነት ይጠቀስ እንደነበር አስታውሰዋል ። በአሁኑ ወቅት ግን የአውሮፓ ህብረት ከሚያወጣቸው የንግድ ገደቦችና ህጎች ጋር ተያይዞ አማራጭ ገበያዎችን ማስፋፋት አስፈላጊ መሆኑን ገልፀዋል። መንግስት አዳዲስና አማራጭ ገበያዎችን ለማስፋፋት የሚያደርገው ጥረት የኤክስፖርት መጠን የሚጨምርና በአንድ ገበያ ላይ ያለንን ጥገኝነት የሚቀንስ በመሆኑ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አብራርተዋል።
የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን በተከናወኑ ተግባራት ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ውጤቶች እየተመዘገቡ ነው
Sep 2, 2026 193
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን በተከናወኑ ተግባራት ሀገራዊ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የግብርና ሚኒስቴር በ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም እና የ2019 ዕቅድ ላይ ግምገማ እያካሄደ ነው። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በ2017/18 የምርት ዘመን የግብርና ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል። በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ የግብርና ግብዓቶች በተሳለጠ መልኩ ተደራሽ መደረጋቸውን በመግለጽ፤ 20 ሚሊየን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሮች ተደራሽ መደረጉን ተናግረዋል። ይህም ለምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥ ዓይነተኛ ሚና ከመጫወቱም ባለፈ ሀገራዊ የማምረት አቅም እያደገ መምጣቱን አመላካች ነው ብለዋል። የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ባህል እየሆነ መምጣቱን ገልጸው፤ ለዚህ ውጤት መገኘት በየደረጃው ያለው የዘርፉ አመራር ቁርጠኝነት ትልቅ ሚና መጫወቱን አንስተዋል። በሌማት ትሩፋት ኤኒሼቲቭ የወተትና የእንቁላል ምርትን በማሳደግ አመርቂ ውጤቶች እየተገኙበት መሆኑን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የደን ሽፋንን ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ እንዲል ማድረግ መቻሉን ገልጸው፤ ይህ የተፋስስ ልማትም ለወጣቶች እና ሴቶች ሰፋፊ የስራ ዕድል በመፍጠር ትልቅ ውጤት የተገኘበት መሆኑን አብራርተዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታዋ ገለጻ፤ ወደ ውጭ ከተላኩ የግብርና ምርቶች 4 ነጥብ 55 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ተገኝቷል። ከዚህ ውስጥ 3 ነጥብ 1 በሊዮን ዶላሩ የተገኘው ከቡና መሆኑን ጠቁመው፤ ለዚህ ደግሞ አረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብር የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። በቀጣዩ በጀት ዓመት በግብርናው ዘርፍ የላቀ ውጤት ለማምጣት ከግብዓት አቅርቦት፣ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በተሻለ መልኩ ለመተግበር መረባረብ አለብን ብለዋል። የዛሬው የግምገማ መድረክም የባለፈው ዓመት አፈጻጸም ላይ በመወያየት ለተሻለ ስኬት አቅጣጫዎችን ለማስቀመጥ ያለመ መሆኑንም ተናግረዋል። በመድረኩ የክልል ግብርና ቢሮ ሃላፊዎች እና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። በበጀት አመቱ ወደ ውጭ ከተላኩ የግብርና ምርቶች 4 ነጥብ 55 ቢሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱ ይታወሳል፡፡