ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተመዘገቡ ውጤቶች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል
Mar 16, 2026 60
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018 (አዜአ)፦ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተመዘገቡ ውጤቶች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሃብት ልማት፣ ሥራ ሥምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በምክር ቤቱ የሰው ሃብት ልማት፣ ሥራ ሥምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴርን የስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ገምግሟል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፤ የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርትን አቅርበዋል። በሪፖርታቸውም፤ ባለፉት ስድስት ወራት በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት ኢንተርፕራይዞችንና የመዳረሻ ሀገራትን በማስፋት ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር እንደተቻለ ገልጸዋል። በዚህም በሀገር ውስጥ ለ2 ነጥብ 7 ሚሊየን ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር በተያዘው ዕቅድ መሰረት በብዝኅ ኢኮኖሚ ዘርፎች ውስጥ 2 ነጥብ 8 ሚሊየን ዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስታውቀዋል። የቋሚ ኮሚቴው አባላትም፤ ባለፉት ስድስት ወራት የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራትንና የቀጣይ ስራዎችን በተመለከተ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ፤ የኢንተርፕራይዞችን የፋይናንስ ፍላጎት ምላሽ መስጠት የሚያስችል አሰራር በመዘርጋት ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ እየተቻለ ነው ብለዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ዳንኤል ተሬሳ፤ የመዳረሻ ሀገራትን በማስፋት ዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በሂደቱም በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት ወቅት ሕጋዊ ግዴታቸውን በማይወጡ ኤጄንሲዎች ላይ ሕጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ እየተወሰደ ነው ብለዋል። የቴክኒክና ሙያ ተቋማት በዕውቀትና ክህሎት የበለጸገ ዜጋ በማፍራት ለሥራ ገበያው ዝግጁ የሆነ የሰው ሃይል እያቀረቡ ነው ያሉት ደግሞ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) ናቸው። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፤ በበጀት ዓመቱ ቀሪ ወራት የክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከል ግንባታን በማጠናቀቅ ዕውቀትና ክህሎትን ያጣመሩ ዜጎች ለማፍራት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር)፤ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት እያከናወነ ነው ብለዋል። በቀጣይም ዘመናዊ የቴክኖሎጂ አቅምን የበለጠ በማጠናከር ዜጎች በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት ተጠቃሚነትን ማስቀጠል እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን ከ970 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ የመንገድ ግንባታና ጥገና ተከናውኗል
Mar 16, 2026 73
ደብረ ማርቆስ፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን ባለፉት ስምንት ወራት ከ970 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ የአዲስ መንገድ ግንባታ፣ ጥገና እና ተያያዥ ተግባራት መከናወናቸውን የዞኑ መንገድ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መምሪያ አስታወቀ። የኮሪደር ልማት ዘመናዊ ከተሜነትን በማስፋፋት ከተሞችን የብልጽግና ማዕከል እያደረገ ነው መምሪያው ባለፉት ስምንት ወራት የተከናወኑ ተግባራትን የሚገመግም መድረክ በደብረ ማርቆስ ከተማ አካሂዷል። በመድረኩ ላይ የመምሪያው ኃላፊ አቶ ማናየ አዳነ እንደገለጹት፤ የመንገድና ትራንስፖርት ዘርፉ ለአገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና ለማህበራዊ ትስስር የጀርባ አጥንት መሆኑን በመገንዘብ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል። በዚህም ከመንግስት፣ ከረድኤት ድርጅቶችና ከማህበረሰቡ በተገኘ ከ970 ሚሊየን ብር በላይ በጀት የተለያዩ ስራዎች ተከናውነዋል ብለዋል። ከተከናወኑ ተግባራት መካከል 652 ኪሎ ሜትር መንገድ የጥገና ሥራ፣ ከ11 ኪሎ ሜትር በላይ አዲስ የጠጠር መንገድ ግንባታ እና 30 ኪሎ ሜትር የውሃ ማፋሰሻ ቦይና ሌሎች ግንባታና ጥገና መካሄዱን ገልጸዋል። እነዚህ የግንባታና የጥገና ሥራዎች በጎዛምን፣ በማቻከል፣ በደብረ ኤሊያስ፣ በሰዴ፣ በባሶ ሊበንና በሌሎችም ወረዳዎች መከናወናቸውን ኃላፊው ጠቁመዋል። የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ዋለ አባተ በበኩላቸው፤ መንግስት ህብረተሰቡንና ባለሀብቶችን በማስተባበር ለመሠረተ ልማት ዝርጋታ ትኩረት መስጠቱን ተናግረዋል። በተለይም በትራንስፖርት ስምሪት ላይ የሚታዩ ብልሹ አሰራሮችንና ሙስናን ለማስወገድ የዲጂታል አሰራርን መተግበር ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። በፌዴራልና በክልል መንግስት ድጋፍ ተጨማሪ የ200 ኪሎ ሜትር መንገድና የሰባት ድልድዮች ግንባታ በአሁኑ ወቅት እየተከናወነ መሆኑም ተገልጿል።
በቅርቡ የጸደቀው አዲሱ የቱሪዝም ፖሊሲ ለብዝሃ ቱሪዝም ዕድገት ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል
Mar 16, 2026 82
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፡-በኢትዮጵያ በቅርቡ የጸደቀው አዲሱ የቱሪዝም ፖሊሲ ለኪነ ጥበብ ቱሪዝም ትኩረት በመስጠት ለብዝሃ ቱሪዝም ዕድገት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የቱሪዝም ሚኒስቴር ገለጸ። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለዛምቤዚ ተፋሰስ አገራት ተሞክሮ የሚሆን ነው በሰዓሊ ተገኔ ኩንቢ በጣሊያን ቬንስ በሚካሄደው 61ኛው የቬኒስ ቢየናሌ የኢትዮጵያን ፓቪሊዮን "የዝምታ ቅርጾች" የተሰኘ አውደ ርዕይ ዙሪያ የቱሪዝም ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን እና የኤግዚቢሽኑ አዘጋጅ ሰዓሊ ተገኔ ቁንቢ በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል። የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ስለሺ ግርማ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለሁለተኛ ጊዜ የምትሳተፍበት የቬኒስ ቢየናሌ በዓለም ላይ ካሉ ጥንታዊና ታዋቂ ዝግጅቶች አንዱ ነው። በኢትዮጵያ ከለውጡ ወዲህ ለብዝሃ ቱሪዝም ዘርፍ ትኩረት በመስጠት አዳዲስና ነባር የቱሪዝም መዳረሻዎችን የማስፋፋት ስራዎች ተከናውነዋል ብለዋል። ቱሪዝም ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የሚኖረውን አበርክቶ ማሳደግ የሚያስችል የቱሪዝም ፖሊሲ መፅደቁንም ገልጸዋል። አዲሱ የቱሪዝም ፖሊሲ ብዝሃ ቱሪዝምን ለማሳደግ ታሪካዊና ባህላዊ የቱሪስት መስህቦችን፣ ኢኮ-ቱሪዝም፣ ጂኦ ቱሪዝም፣ የቡና ቱሪዝም፣ ኮንፍረንስ ቱሪዝም እና የአርት/የኪነ ጥበብ ቱሪዝም ዘርፎችን አካቷል ብለዋል። ኢትዮጵያ በጣሊያን ቬኒስ ከተማ በሚካሄው ዓለም አቀፍ ዝግጅት የኢትዮጵያ ፖቪሊዮን "የዝምታ ቅርጾች" በማዘጋጀት የኪነ ጥበብ ስራዎቿን የምታስተዋውቅበት መድረክ መሆኑን ገልፀዋል። ይሄውም አዲሱ የቱሪዝም ፖሊሲ ለብዝሃ ቱሪዝም የሰጠውን ትኩረት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸው፤ ኤግዚቢሽኑ ዓለም አቀፍ የሥዕል ሥራዎችን ውድድር ያለፉ አርቲስቶች ቀርበው የሀገራቸውን ገፅታ የሚገነቡበትና የሚያስተዋውቁበት መድረክ ነው ብለዋል። መድረኩ የኢትዮጵያን የኪነ ጥበብ ሥራዎች ለዓለም ለማስተዋወቅ የሚያስችል መሆኑን በማንሳት፤ የኢትዮጵያን ልዩ የሙዚቃ፣ ስዕልና ቴአትር ጥበብ እንደሚያሳይ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር አበባው አያሌው፤ ኢትዮጵያ በኪነ ጥበብ ሥራዎች ባላት ዕምቅ አቅም ልክ ተጠቃሚ አልነበረችም ብለዋል። ይሁን እንጂ ከለውጡ ወዲህ ባለው የአስር ዓመት መሪ የልማት ዕቅድ ኪነ ጥበብ ስራዎች ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ሰዓሊ ተገኔ ቁንቢ ያዘጋጀው አውደ ርዕይ "ዝምታ" የኢትዮጵያን ማህበራዊና ፖለቲካዊ ሁኔታ የሚያቀርብ መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ በስዕልና ቅርፃ ቅርፅ ዘርፍ ያሉ ሰዎች በስፋት እንዲሳተፉ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸው፤ ለሌሎች አርአያ የሚሆን ስኬታማ ስራ ነውም ብለዋል። አውደ ርዕዩ የኢትዮጵያ አመለካከትና ፈጠራ የተገለጠበት ድንቅ ዝግጅት መሆኑን ገልጸዋል። "የዝምታ ቅርጾች" አውደ ርዕይ አዘጋጅ ሰዓሊ ተገኔ ቁንቢ፤ ዝምታ ባዶ ሳይሆን በውስጡ የታመቀ ሀሳብ ያለው ነው ብለዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ነጠላ የኢኮኖሚ አተያይን ወደ ብዝኅ ዘርፍ በማሸጋገር እመርታዊ ዕድገት እንዲመዘገብ እያስቻለ ነው
Mar 16, 2026 70
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ነጠላ የኢኮኖሚ አተያይን ወደ ብዝኅ ዘርፍ በማሸጋገር እመርታዊ ዕድገት እንዲመዘገብ እያስቻለ መሆኑ ተገለጸ። በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎትና በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ትብብር "ኢትዮጵያ - አዲሲቷ የኢንቨስትመንት መዳረሻ" በሚል መሪ ሃሳብ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርሙ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ፍሰትን እያሳደገ ነው በውይይቱ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ በረከት ፍስሃ-ፅዮን፤ ሀገራዊ ለውጡ የኢትዮጵያን ውስን የኢኮኖሚ አተያይ ወደ ብዝኅ ዘርፍ የልማት አቅጣጫ ማሸጋገር አስችሏል ብለዋል። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያም የነጠላ ዘርፍ ኢኮኖሚን በብዝኅ አተያይ በመቀየር አስተማማኝ የዕድገት ምኅዳር እንዲፈጠር ማድረጉን ገልጸዋል። ይህም የንግድና ኢንቨስትመንት አማራጮችና የልማት አቅሞች በብዛትና በጥራት የሚስፋፉበትን ምቹ የዕድገት መደላድል መፍጠር እንዳስቻለ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የኢንቨስትመንት ፍሰትና ተወዳዳሪነትን እያሳደገ ነው ብለዋል። የኢንቨስትመንት ዘርፍ ስኬቶች ተገማችና ጥራት ያለው የኢኮኖሚ ምኅዳር በመፍጠር በተኪ ምርትና በሥራ ዕድል ፈጠራ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያሻሻለ መሆኑን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍጹም ከተማ በበኩላቸው፤ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ እመርታዊ የፖሊሲና የአሰራር ምኅዳር እንዲፈጠር አድርጓል ብለዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኮችም የምርታማነት አቅምን በማሳደግ በሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ የሚኖራቸውን ድርሻ በማጎልበት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ኢትዮጵያን ምቹ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት የስበት ማዕከል እያደረጋት ይገኛል ያሉት ደግሞ የገዳ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ዋና ስራ አስፈጻሚ ሞቱማ ተመስገን ናቸው፡፡ የኢንዱስትሪ ፓርኮችም ወደ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን የሚሸጋገሩበትን አስቻይ ምኅዳር በመፍጠር ጥራትና ብቃት ያላቸው አልሚዎች መዋለ ነዋያቸውን ፈሰስ የሚያደርጉበትን ዕድል እንደፈጠረ ገልጸዋል፡፡ የሞሐን ግሩፕ ኩባንያዎች ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሀርሽ ኮታሪ፤ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የአልሚ ባለሃብቶችን ትርፋማነት በማሻሻል ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢ መፍጠሩን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሰይፈ ደርቤ በበኩላቸው፤ በሀገራዊ ለውጡ ማግስት የመገናኛ ብዙኅን የኢትዮጵያን ምቹ የኢንቨስትመንት አማራጭ የሚገልጡበትን ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። በዚህም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ሥራ የጀመረው የፐልስ ኦፍ አፍሪካን (POA) ጨምሮ የህዝብና የንግድ መገናኛ ብዙኅን የሀገርን የዕድገት ዕድሎች እያስተዋወቁ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በቀጣይም መገናኛ ብዙኅን በተለያዩ የቋንቋ አማራጮች ኢንቨስትመንትን ለማነቃቃት የሚያበረክቱትን ጉልህ አስተዋጽኦ ለማስቀጠል የመረጃ ሰጪ ተቋማት ትብብር ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ተናግረዋል። የፓናል ውይይቱ ተሳታፊዎች በበኩላቸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ ለቴክኖሎጂ ትልቅ ትኩረት የሰጠ እና የኢትዮጵያን የእድገት ግስጋሴ የሚያፋጥን አቀጣጣይ ሞተር መሆኑን ተናግረዋል።
ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም በተለያዩ ዘርፎች ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል- ምሁራን
Mar 16, 2026 123
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018(ኢዜአ)፡-ለውጡን ተከትሎ መንግሥት ተግባራዊ ያደረገው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም የምርት መጠንን በማሳደግና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን በማሻሻል ረገድ ከፍተኛ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን የተለያዩ የኢኮኖሚ ምሁራን ገለጹ። ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርሙ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ፍሰትን እያሳደገ ነው መንግሥት የተከተለው የብዝሃ-ዘርፍ ኢኮኖሚ ስትራቴጂም ኢኮኖሚው በአንድ ዘርፍ ላይ ብቻ ጥገኛ እንዳይሆን በማድረግ ለዘላቂ ሀገራዊ ዕድገት አስተማማኝ መሠረት መጣሉንም ገልጸዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የኢኮኖሚ ምሁራን እንደገለጹት፣ በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረገው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም እና የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ነባር መዋቅራዊ ተግዳሮቶችን በመፍታትና የገበያ መረጋጋትን በማምጣት ረገድ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። በኢትዮጵያ ፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ከፍተኛ ተመራማሪ ጀማል መሀመድ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ ከለውጡ በፊት በነበረው የኢኮኖሚ መዋቅር የውጭ ኩባንያዎች በሀገሪቱ የልማት እንቅስቃሴ ላይ ያላቸው ተሳትፎ የተገደበ ነበር። ይህም ዓለም አቀፍ ባለሀብቶች ሰፊ የገበያ ዕድሎችን እንዳያገኙና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ፍሰት እንዲቀዘቅዝ ከፍተኛ ተጽዕኖ ማሳደሩን ገልፀዋል። በመሆኑም ሀገሪቱ በውጭ ምንዛሬ እጥረትና በከፍተኛ የዕዳ ጫና ውስጥ እንድትቆይ ምክንያት መሆኑን አስረድተዋል። ለውጡን ተከትሎ ቀደም ሲል የነበሩት የፖሊሲ ማነቆዎች ተወግደው በምትኩ ምቹ ምህዳር መፈጠሩ የኢኮኖሚውን ተወዳዳሪነት ለማሳደግና የግል ዘርፉን ለማነቃቃት ወሳኝ ሚና መጫወቱን ተናግረዋል። ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም እንደ ቴሌኮሙኒኬሽን፣ የባንክ አገልግሎት፣ የችርቻሮ ንግድ እና የኮንስትራክሽን ዘርፎችን ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት በማድረግ አዲስ የገበያ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። የዚህ ሪፎርም ትግበራ እንደ ሳፋሪኮም ያሉ ግዙፍ የዓለም አቀፍ ተቋማት በኢትዮጵያ ውስጥ በስፋት ኢንቨስት እንዲያደርጉ አስችሏል ብለዋል። በእነዚህ ስትራቴጂካዊ ዘርፎች ውስጥ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች በንቃት መሳተፍ መቻላቸው የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማፋጠን፣ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ እና በሀገር ውስጥ ያለውን የአገልግሎት ጥራትና ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ከፍተኛ ፋይዳ ማስገኘቱን ጠቁመዋል። በሪፎርሙ የውጭ ምንዛሬ በገበያ እንዲወሰን መደረጉ፣ የመንግሥት ገቢና ወጪን የማመጣጠን ስራ እና የታክስ መሰረቱን ማስፋት ለኢኮኖሚው ስኬት ትልቅ መገለጫዎች መሆናቸውን አንስተዋል። በተለይም ለማዕድን ዘርፍ በተሰጠው ልዩ ትኩረት በወርቅ ምርትና ግብይት ላይ የተመዘገቡ ውጤቶች የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ግኝት በማሳደግ ረገድ ጉልህ ሚና ተጫውተዋል ብለዋል። በኢትዮጵያ ኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበር ከፍተኛ ተመራማሪ ሞላ አለማየሁ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ በሪፎርሙ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን የሚያበረታቱ ፖሊሲዎች መተግበራቸውን ገልጸዋል። ይህም የውጭ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ያላቸውን ተሳትፎ በከፍተኛ ደረጃ እያሳደገው መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም በኢትዮጵያ የፋይናንስ ዘርፉን ዲጂታላይዝ ማድረግ መቻሉ፣ ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን የኢኮኖሚ ተወዳዳሪነት እያሳደገው መሆኑን ጠቁመዋል።
የወረዳው አርሶ አደሮች በበልግ ወቅት እርሻ ስራ ውጤታማ ለመሆን በትጋት እየሰሩ ነው
Mar 16, 2026 76
ሀላባ ቁሊቶ ፤መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ):- በበልግ ወቅት እርሻ ስራ ውጤታማ ለመሆን ጠንክረው እየሰሩ መሆኑን በሀላባ ዞን የዌራ ዲጆ ወረዳ አርሶ አደሮች ተናገሩ። የሀላባ ዞን ግብርና መምሪያ በበኩሉ በዞኑ በበልግ ወቅት እርሻ ከ39 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ በማልማት ከ1 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ እየተሰራ ነው ብሏል። በዞኑ የዌራ ዲጆ ወረዳ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ እየጣለ ያለውን ዝናብ በአግባቡ ተጠቅመው በበልግ ወቅት እርሻ ውጤታማ ለመሆን ጠንክረው እየሰሩ ነው፡፡ በዞኑ የዌራ ዲጆ ወረዳ የሲንብጣ ቀበሌ አርሶ አደር ጀማል ሀሰን በበልግ እርሻ በ1 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ላይ በቆሎ፣ ስንዴ፣ ዳጉሳና ሌሎችን ለመዝራት አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም አሁን ላይ እየጣለ ያለውን ዝናብ በአግባቡ ለመጠቀም መሬትን ደጋግሞ በማረስ ውጤታማ ለመሆን እየሰሩ እንዳለ ጠቅሰው ለዚሁ የሚሆን ዘርና ማዳበሪያ ማግኘታቸውንም ገልጸዋል። በወረዳው የበሸኖ ቀበሌ አርሶ አደር ሀቢብ ጉጄ በበኩላቸው ባላቸው ከ2 ሄክታር በላይ ማሳ የበልጉን ዝናብ በመጠቀም በቆሎና ቦሎቄ ለመዝራት ቅድመ ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የዘንድሮው የበልግ ዝናብ ቀድሞ መግባቱ የበለጠ እንዳነሳሳቸው ጠቅሰው የተሻለ ምርት ለማግኘት የተፈጥሮ ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘርና ሌሎች ግብዓቶችን በመጠቀም ዝግጅት እያደረጉ እንደሆነ ተናግረዋል። የሚያመርቱትን ምርት ከቤት ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ ለመሆን በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ ታግዘው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በወረዳው በበልግ ከ10 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በኩታ-ገጠም ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ያነሱት ደግሞ የወረዳው የግብርና ጽህፈት ቤት ምክትልና እርሻ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ሪባቶ ቃባቶ ናቸው። በዚህም ከ678 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ግብ መጣሉን ጠቅሰው ይህን ለማሳካትም በቂ ግብዓት መቅረቡንና የግብርና ባለሙያዎች ደግሞ በተቀናጀ መልኩ ድጋፍና ክትትል እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዞኑ በመደበኛው የበልግ ወቅት እርሻ ከ39 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከ1 ነጥብ 9 ሚሊዮን በላይ ኩንታል ምርት ለማግኘት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የሀላባ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሀጂ ኑሪዬ ናቸው ። የዝናብ ውሃና እርጥበትን በመጠቀም ውጤታማ ለመሆን በተቀናጀ መንገድ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው ከ22 በላይ ቀበሌዎች እርጥበትን በመጠቀም የቅድመ በልግ እርሻ መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ በዞኑ ለማልማት ከታቀደው መሬት 60 በመቶው በክላስተር እንደሚለማ የጠቀሱት ኃላፊው ይህም ቴክኖሎጂና ግብዓትን አቀናጅቶ በመጠቀም ውጤታማ ለመሆን እንደሚያግዝም አመልክተዋል፡፡
በጋሞ ዞን በመሬት መንሸራተት አደጋ ለተጎዱ ወገኖች ሰብአዊ ድጋፍ ከማድረግ ጎን ለጎን መልሶ ለማቋቋም በቅንጅት እየተሰራ ነው- የዞኑ አስተዳደር
Mar 16, 2026 94
አርባ ምንጭ ፤መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፡-በጋሞ ዞን በመሬት መንሸራተት አደጋ ለተጎዱ ወገኖች ሰብአዊ ድጋፍ ከማድረግ ጎን ለጎን መልሶ ለማቋቋም በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ፡፡ አስተዳደሩ አደጋው ከተከተበት ጊዜ አንስቶ ለተጎዱ ወገኞች በተለያየ መንገድ ድጋፍ ያደረጉ አካላትንም አመስግኗል፡፡ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ደምስ አድማሱ (ዶ/ር) ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ እንዳሉት፣ በዞኑ በተለያዩ ወረዳዎች በተከሰተ የመሬት መንሸራተት አደጋ በሰው ሕይወትና በንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ደርሷል። በዚህም የሰው ህይወት መጥፋቱንና ከቀዬአቸው የተፈናቀሉ ወገኖች በጊዜያዊ መጠለያ እንደሚገኙ ገልጸው፣ለተጎጂዎች ሰብአዊ ድጋፍ ከማድረግ ጎን ለጎን መልሶ ለማቋቋም በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደን ጨምሮ በየደረጃው ያሉ የሥራ ሃላፊዎች ተጎጂዎችን ከማጽናናት ባለፈ በቀጣይ ለሚሰሩ ሥራዎች በቅርበት እየደገፉ መሆኑንም ገልጸዋል። በእስካሁኑ ሂደት በየደረጃው ያሉ የመንግስት መዋቅሮችን ጨምሮ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና ባለሃብቶች ላደረጉት ሰብአዊ ድጋፍም ደምስ (ዶ/ር) አመስግነዋል፡፡ የዞኑ አስተዳደር ተጎጂዎችን መልሶ ለማቋቋም ከክልል እስከ ፌደራል ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር እየሠራ መሆኑን ጠቅሰው ፣ ድጋፉ ቀጥታ ለተጎጂዎች እንዲደርስም በልዩ ትኩረት እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። ለወገን ደራሽ ወገን በመሆኑ በመልሶ ማቋቋም ሥራው በሀገር ውስጥና በውጭ ያሉ ወገኖች ድጋፍ እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርበዋል። የአካባቢው መልክዓ ምድር አቀማመጥ ለትራንስፖርት አዳጋች ቢሆንም የተለያዩ የማጓጓዣ አማራጮችን በመጠቀም ድጋፉን ለተፈናቃይ ወገኖች የማድረስና የመንገድ ጥገና ስራም እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ለተፈናቀሉ ወገኖች የሚደረግ ሰብአዊ ድጋፍና መልሶ የማቋቋም ሥራ በቅንጅት እየተከናወነ መሆኑ መግለጻቸውም ይታወሳል።
በሐረሪ ክልል ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይትን በሚፈጽሙ ማደያዎች ላይ ህጋዊ እርምጃ ይወሰዳል
Mar 16, 2026 115
ሐረር፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፡- በሐረሪ ክልል ህገ ወጥ የነዳጅ ግብይትን በሚፈጽሙ ማደያዎች ላይ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ የክልሉ ኢንተርፕራይዞች ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ አስታወቀ። ነዳጅን በቁጠባ፣ ለመሠረታዊ ነገሮች ቅድሚያ በመስጠት በኃላፊነት ስሜት መጠቀም እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዛሬ ማሳሰባቸው ይታወሳል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የነዳጅ አከፋፋዮች፣ ማደያዎች እና ሌሎች ተጠቃሚዎች ነዳጅን በቁጠባ እንዲጠቀሙ መልዕክት አስተላልፈዋል። ይህንንም በተመለከተ ቢሮው በሐረሪ ክልል በነዳጅ ግብይት ላይ የሚስተዋሉ ህገ-ወጥ ተግባራትን መከላከል በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ውይይት አድርጓል። የክልሉ ኢንተርፕራይዞች ልማትና ኢንዳስትሪ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡስማኢል ዩስፍ እንደተናገሩት፤ በክልሉ ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ግብረ ሃይል ተቋቁሞ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። በመሆኑም መንግስት በከፍተኛ ድጎማ ወደ ሀገር የሚያስገባውን ነዳጅ ለመሰረታዊ ጉዳይ ከማዋል ይልቅ በአቋራጭ ለመበልጸግ በሚሹ አካላት የሚደረጉ ህገ- ወጥ ተግባራትን ለመከላከል በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በተለይ ከነዳጅ ማደያ ውጪ ግብይት የሚፈጽሙ፣ ከተቀመጠው ታሪፍ በላይ የሚሸጡ እና ሌሎች ተያያዥ ህገ-ወጥ ተግባራት የሚያከናውኑ የነዳጅ ማደያዎች መኖራቸው እንደተደረሰበት አንስተዋል። እንዲሁም አንዳንድ ማደያዎች የነዳጅ ምርትን በሕጋዊ ሥርዓት እንዳይሰራጭ በማድረግ ሕገ-ወጥ ተግባር እንደሚፈጽሙ አንስተዋል። ደንበኞችን በማጉላላት ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይት የሚፈጽሙ አካላት መኖራቸውን ጠቁመው በዚህ እና መሰል ተግባራት ላይ የተሰማሩ የነዳጅ ማደያዎች ከድርጊታቸው በመቆጠብ ህግና መመሪያን አክብረው እንዲሰሩ አሳስበዋል። ከተቀመጠው አሰራር ውጪ ሲተገብሩ በሚገኙ የነዳጅ ማደያዎች ላይ ጠንካራ፣ ህጋዊና አስተዳደራዊ የእርምት እርምጃ እንደሚወሰድም አስጠንቅቀዋል። የሐረሪ ክልል ፖሊስ ኮሚሽነር አህመድ አብዲ በበኩላቸው፤ በክልሉ በነዳጅ ግብይት ላይ የሚከናወኑ ህገ-ወጥ ግብይትና ሌሎች ተያያዥ ተግባራትን የመከታተልና የመቆጣጠሩ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በዚህም በዘርፉ የተሰማሩ አካላት በአግባቡ ግብይት ሊፈፅሙ እንደሚገባ ጠቁመው በተለይ የትብብርና ቅንጅት አሰራሮችን ማጠናከር እንደሚገባም አመልክተዋል። በመድረኩ ከተገኙት የነዳጅ ማደያ ባለቤቶች መካከል አቶ ፎዚ ያህያ እንደተናገሩት፤ አላስፈላጊ ጥቅም ለማግኘት ሲባል የሚከናወነውን ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይት የመከላከሉን ተግባር እንደሚያጠናክሩም ተናግረዋል። ሌላው ተሳታፊ አቶ አብዱሽኩር ጃሚ በበኩላቸው፤ አሰራርን መሰረት ያደረገ የግብይት ስርዓትን እንደሚከተሉና ይህንንም ከቢሮው ጋር በመቀናጀት እንደሚተገብሩት አመልክተዋል።
የሙያ ማሕበራት ለመጀመሪያ ደረጃ የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት የላቀ ሚናቸውን ማጠናከር አለባቸው
Mar 16, 2026 75
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018(ኢዜአ)፦የሙያ ማሕበራት ለመጀመሪያ ደረጃ የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነት የላቀ ሚናቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ ገለጹ፡፡ ከመጋቢት 6 እስከ 8 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየው የኢትዮጵያ ጤና አጠባበቅ ማህበር 37ኛ ዓመታዊ ኮንፍረንስ ማስጀመርያ መርሃ ግብር ተካሂዷል። የጤና ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ መንግሥት የጤና ስርዓቱን ለማዘመን በዘርፉ ከተሰማሩ ባለሙያዎችና ማህበራት ጋር በቅርበት እየሰራ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ጤና አጠባበቅ ማህበር በመላው ኢትዮጵያ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶችን በመክፈት ማህበረሰቡን በስፋት እያገለገለ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለዚህም ምስጋና ይገባዋል ብለዋል፡፡ ማህበሩ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በመተባበር ችግር ፈቺ ጥናትና ምርምር በማከናወን ረገድ የሚጫወተው ሚና የላቀ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ጤና አጠባበቅ ማህበር የጥናትና ምርምር ውጤቶች ለመንግሥት ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎችና ዕቅዶች ግብዓትነት ጥቅም ላይ እየዋሉ ነው ብለዋል፡፡ የጥናትና ምርምር ውጤቶች የኢትዮጵያን አቅም በማሳየት ለዓለም አቀፉ የጤና አጠባበቅ ሥርዓት ገንቢ ሚና እየተወጣ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ መንግሥት የጤና ሥርዓቱን ለማዘመን በሚያደርገው ጥረት ማህበሩ ለጤና ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና በመስጠት እገዛ እያደረገ መሆኑን ገልጸው፤ ከኤች አይ ቪ/ኤድስ፣ የእናቶችና ህፃናት ጤና አጠባበቅ እና በቤተሰብ ዕቅድ አገልግሎት ዙሪያ ወሳኝ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ማህበሩ የዜጎችን የጤና ፍላጎት፣ ጥራትና ተደራኝነት እንዲሁም ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በመጀመሪያ የጤና አገልግሎት አሃድ ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡ የሙያ ማሕበራት መንግሥት የመጀመሪያ ደረጃ የጤና አገልግሎትን ጥራትና ተደራሽነት ለማሳደግ በሚያደርገው ጥረት ገንቢ ሚናቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጠይቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ጤና አጠባበቅ ማህበር ፕሬዝዳንት ዶክተር አጎናፍር ተካልኝ በበኩላቸው፤ ሁሉን አቀፍ የጤና ተደራሽነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ማህበሩ ከ10 ሺህ በላይ አባላት እንዳሉት ገልጸው፤ የባለሙያዎችን አቅም በመገንባትና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡ 37ኛው ዓመታዊ ኮንፍረንስ መንግስት የጤና ጥራትና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ የሚያደርገውን ጥረት መደገፍ ላይ ያተኮረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመርሃ ግብሩ በጤና ተደራሽነት ዙሪያ የጥናትና ምርምር ስራዎችን ያከናወኑ፣በጤናው ዘርፍ ንቁ ተሳትፎ ያደረጉ ግለሰቦችና ተቋማት እውቅና እና የሜዳልያ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርሙ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ፍሰትን እያሳደገ ነው
Mar 16, 2026 169
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ፍሰትን እያሳደገ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ጋር በመተባበር" ኢትዮጵያ - አዲሲቷ የኢንቨስትመንት መዳረሻ" በሚል መሪ ሐሳብ የምክክር መድረክ እያካሄደ ይገኛል። በመድረኩ ላይ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የንግድና ቱሪዝም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዮሐንስ መስፍን፣ እንዲሁም የፌደራልና የክልል የኢንቨስትመንት ልማት ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። የኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ ባቀረቡት መነሻ ጽሑፍ መንግሥት የጀመረው የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ያለውን ሰፊ አማራጭ ተመልክተው በስፋት እንዲሰማሩ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። ማሻሻያው የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት እንዲሳብባቸው ተለይተው በተቀመጡ አምስት ቁልፍ የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ትልቅ መነቃቃትን መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡ በዚህም አዳዲስ ባለሀብቶች መግባታቸው ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለቴክኖሎጂ ሽግግር ከፍተኛ ፋይዳ እያበረከተ እንደሚገኝም ነው የገለጹት፡፡ ሪፎርሙ በተለያዩ ዘርፎች ላይ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን ጠቁመው የሀገሪቱን የተፈጥሮ ሀብት በቴክኖሎጂ በማልማት ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም ጠቅሰዋል፡፡ በቱሪዝም፣ አይ ሲቲ እና ዲጂታል ኢኮኖሚ ዘርፎች መንግሥት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ዘመናዊና ዲጂታል ኢኮኖሚን በመገንባት ኢንቨስትመንት የመሳብ ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። ከዚህ ቀደም ዝግ የነበረው የቤት ልማት ዘርፍ በሕግ ማሻሻያ አማካኝነት ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት መሆኑንም አስታውቀዋል። ኮሚሽኑ ባከናወነው የተቀናጀ የማስተዋወቅ ሥራ አመርቂ ውጤት መመዝገቡን የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ ከ2013 ዓ.ም እስከ 2017 ዓ.ም ዓመታት ውስጥ 18 ነጥብ 6 ቢሊየን ዶላር የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ ነፃ ንግድ ቀጣናዎች ለውጭ ባለሀብቶች ምቹ የሥነ-ምኅዳር ዕድል መፍጠራቸውን ጠቁመው፤ በቀጣይም ሀገሪቱ በአህጉሪቱ ያላትን የኢንቨስትመንት ደረጃ ይበልጥ ለማሻሻል በትኩረት እንደሚሠራ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያን የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ተወዳዳሪነት የሚያጎለብት ምቹ ምኅዳር ተፈጥሯል-ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)
Mar 16, 2026 144
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት የተወዳዳሪነት አቅምን የሚያጎለብት ምቹ ምኅዳር መፈጠሩን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ጋር በመተባበር "ኢትዮጵያ - አዲሲቷ የኢንቨስትመንት መዳረሻ" በሚል መሪ ሃሳብ የምክክር መድረክ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፣ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የንግድና ቱሪዝም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዮሐንስ መስፍን፣ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር)፣ የፌደራልና የክልል የኢንቨስትመንት ልማት ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። በዚሁ ጊዜ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፤ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት የሀገር ውስጥ ቀጣይነት ያለው ዕድገትን ለማሳለጥ ወሳኝ ሚና አለው ብለዋል። በውጭ የኢንቨስትመንት መዕዋለ ነዋያቸውን ፈሰስ የሚያደርጉ ኩባንያዎች ከገንዘብ ባሻገር የዕውቀት፣ ክህሎትና ሰፊ የሥራ ዕድል በማምጣት ሀገራዊ ኢኮኖሚ ዕድገትን እንደሚያፋጥን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ከናይጀሪያ በመቀጠል ብዙ ህዝብ የሚኖርባት ሁለተኛዋ የአፍሪካ ሀገር ናት፤ በከርሰ ምድርና ገጸ ምድር ሃብት የታደለችውን ዕምቅ ሃብትም በውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ማልማት ያስፈልጋል ብለዋል። የኢትዮጵያን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ለማስቀጠልም የውጭ ሃብት ፍሰትን በስፋትና ጥራት ማቅረብ እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያን የብዝኅ ኢኮኖሚ ሥርዓት በኢንቨስትመንት ምኅዳሩ ላይ ከፍተኛ መነቃቃት በመፍጠር ጠንካራና ዘላቂ ልማትና ዕድገት እንዲመዘገብ እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል። የብዝኅ የኢኮኖሚ ሥርዓት ውጤታማነቱም ኢትዮጵያን የአፍሪካ ባለግዙፍ የኢኮኖሚ ባለቤት እያደረጋት እንደሚገኝ አስረድተዋል። በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም ትግበራውም የግሉን ዘርፍ የኢኮኖሚ ተሳትፎ በማሳደግ በኢትዮጵያ የዕድገት ጉዞ የድርሻቸውን የሚወጡበት አስቻይ ሁኔታ መፍጠሩን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት ትግበራም አስተማማኝ፣ ተገማችና የኢንቨስትመንትና የገበያ ከባቢን እየፈጠረ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት በወሳኝ ምዕራፍ መገኘትና የጂኦ-ፖለቲካዊ አመችነት የኢንቨስትመንት ስበትን በማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል። የመደመር መንግሥት ሰላማዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከፍትሐዊ ባሻገር ኢትዮጵያ በቀጣናው የሚኖራትን የንግድና ኢንቨስትመንት ተወዳዳሪነት የበለጠ ለማሳደግ አቅም እንደሚኖረው ተናግረዋል። በተጨማሪም አንጋፋው የኢትዮጵያ አየር መንገድም የኢትዮጵያን ምርቶች ለዓለም ገበያ በማቅረብ ወሳኝ ሚና እንዳለው አንስተዋል። የኢትዮጵያ የካፒታል ገበያም ነባርና አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ተጨማሪ ካፒታል የሚያገኙበትን ዕድል በመፍጠር እና የገበያ ትስስርን በማጠናከር ከፍተኛ የውጭ ሃብት ፍሰትን ለማጠናከር ጉለህ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተዋል። የኢትዮጵያን ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢን የመፍጠር ወሳኝ የሪፎርም እርምጃዎች ስኬታማነት አጠናክሮ ለማስቀጠልም መገናኛ ብዙኅን የሚጠበቅባቸውን ከፍተኛ ኃላፊነት መወጣት እንዳለባቸው አንስተዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሰይፈ ደርቤ፤ ኢዜአ ካለፉት ሰማኒያ አራት ዓመታት አንስቶ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅምና ሀገራዊ መግባባት የአጀንዳ ጉዳዮች ዙሪያ በሀገር ውስጥና በውጭ ቋንቋዎች በትኩረት እየሰራ የሚገኝ ተቋም ነው ብለዋል። በውጭ በእንግሊዝኛ፣ አረብኛና ፈረንሳይኛ እንዲሁም በአምስት የሀገር ውስጥ ቋንቋዎች መረጃዎችን በማሰባሰብ ለሕብረ ብሔራዊ አንድነትና ሀገራዊ መግባባት ዜናና ዜና ነክ ጉዳዮች ላይ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዜናና ዜና ነክ ጉዳዮች የሚሰሩ ዘገባዎችም ከኢዜአ የመረጃ ማሰራጫ ዘዴዎች በተጨማሪ ለሀገር ውስጥና ለበርካታ የውጭ መገናኝ ብዙኅን መረጃን በማመንጨት እያዳረሰ መሆኑን ተናግረዋል። ከኢንቨስትመንት ኮሚሽን ጋር በመተባበር የኢትዮጵያን ምቹ የኢንቨስትመንት መዳረሻነት ለማስተዋወቅ "ኢትዮጵያ - አዲሲቷ የኢንቨስትመንት መዳረሻ" በሚል መሪ ሃሳብ የምክክር መድረክ መዘጋጀቱን አንስተዋል። መድረኩም የኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት ምኅዳር በማስፋት የተገኙ ውጤቶችንና ቀጣይ ትልሞችን በማስተዋወቅ ጉልህ ፋይዳ እንዳለው አንስተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በዞኖቹ በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ተስፋ ሰጪ ውጤት እየተመዘገበ ነው
Mar 16, 2026 69
አምቦ/ጭሮ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ እና ምዕራብ ሐረርጌ ዞኖች በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ተስፋ ሰጪ ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑ ተገለጸ። በምዕራብ ሸዋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት የመስኖ ኤክስቴንሽን ባለሙያ አቶ ቢቂላ ጉቱ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በዞኑ በዘንድሮው የበጋ ወቅት 408 ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ሥራ የተገባ ሲሆን እስካሁን ከ388 ሺህ ሄክታር በላይ በዘር ተሸፍኗል። በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥ በ21 ወረዳዎች ከ147 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም እየለማ ሲሆን ከዚህም 15 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የስንዴ ምርት እንደሚጠበቅም ገልጸዋል። ለአርሶ አደሩ ግብዓት የማቅረብ፣አረም የማስወገድ እና የተባይ መከላከል ሥራዎች የባለሙያዎች ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። በተመሳሳይም በምዕራብ ሐረርጌ ዞን በ15 ወረዳዎች ውስጥ ከ58 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና እና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። በፅህፈት ቤቱ የስንዴ ልማት አስተባባሪ አቶ ሀቢብ አብዱልከሪም በልማት ስራው ከ97 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ ሲሆን 2 ሺህ የሚጠጉ የውኃ መሳቢያ ሞተሮች ተከፋፍለዋል ብለዋል። በዞኑ በአጠቃላይ 3 ሚሊዮን ኩንታል ገደማ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዷል ነው ያሉት። በምዕራብ ሸዋ ዞን በኢሉ ገላን ወረዳ በልማቱ የተሰማሩ አርሶ አደሮች እንደሚሉት፣ ከግብርና ባለሙያዎች በሚያገኙት ምክር በመታገዝ ለማሳቸው ተገቢውን እንክብካቤ እያደረጉ ነው። አርሶ አደር ብርሃኑ ልኩማ "በቂ ማዳበሪያና የተሻሻለ ዝርያ በመጠቀሜ የተሻለ ምርት አገኛለሁ ብዬ እጠብቃለሁ፤ ይህም ኑሮዬን ለማሻሻል ይረዳኛል" ብለዋል። ሌላው አርሶ አደር ገዛኸኝ ደረሰ፣ ቀደም ሲል በክረምት ብቻ ይታረስ የነበረውን ልምድ በመቀየር፣ አሁን በመስኖ በማልማታቸው የገቢያቸው መጠን በእጥፍ እንደሚያድግ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። አርሶ አደሮቹ ከአንድ ሄክታር መሬት ከ25 እስከ 30 ኩንታል ምርት ለማግኘት አቅደው እየሠሩ ይገኛሉ። የምዕራብ ሀረርጌ ዞን ጡሎ ወረዳ የኢፋ አንዶዴ ቀበሌ አርሶ አደር ሲራጅ ዓሊ፣ በሞተር በመታገዝ በዓመት ሁለት ጊዜ ማምረት መጀመራቸውን ገልጸው፣ ከልማቱ የሚያገኙት ገቢ ማዳበሪያ ለመግዛትና ሥራቸውን ለማስፋፋት እንደረዳቸው ተናግረዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ነዳጅን በቁጠባና ለመሠረታዊ ነገሮች ቅድሚያ በመስጠት መጠቀም እንደሚገባ አሳሰቡ
Mar 16, 2026 137
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፡- የነዳጅ አከፋፋዮች፣ ማደያዎች እና ተጠቃሚዎች ነዳጅን በቁጠባ ለመሠረታዊ ነገሮች ቅድሚያ በመስጠት በኃላፊነት ስሜት እንዲጠቀሙ አሳሰቡ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትሥሥር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በመካከላኛው ምሥራቅ በተፈጠረው ቀውስ የተነሣ ነዳጅ ገዝተው የሚጠቀሙ ሀገሮች እንደልብ ለማግኘት ተቸግረዋል ብለዋል። በመሆኑም ችግሩ ተፈትቶ ወደ መደበኛው የነዳጅ አቅርቦት ሥርዓት እስከምንመለስ ድረስ ነዳጅን በቁጠባና ለመሠረታዊ ነገሮች ቅድሚያ በመስጠት መጠቀም ይኖርብናል ነው ያሉት። በመሆኑም የነዳጅ አከፋፋዮች፣ ማደያዎች እና ተጠቃሚዎች ነዳጅን በቁጠባ ለመሠረታዊ ነገሮች ቅድሚያ በመስጠት ሁላችንም በኃላፊነት ስሜት እንድንጠቀም ለማሳሰብ እወዳለው ብለዋል በመልዕክታቸው።
በክልሉ የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት የተጀመሩ ተግባራት ይጠናከራሉ
Mar 15, 2026 117
ባህርዳር ፤ መጋቢት 6 /2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ለ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የላቀ ሀገራዊ ራዕይን በሚያሳካ መልኩ ዝግጅት እየተደረገ ነው የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ አጀበ ስንሻው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የክልሉን የሰብል ምርታማነት በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ። በዚህም ለመጪው የምርት ዘመን ከ8 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ግዢ በመፈጸም ከ3 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሚሆነው ወደ ወደብ መድረሱን ገልጸዋል። ወደብ ከደረሰው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥም እስካሁን ከ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የሚሆነውን ወደ ክልሉ በማስገባት የማሰራጨት ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። እየቀረበ ያለው የአፈር ማዳበሪያም የሰብል ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የሚያስችል መሆኑንም አመልክተዋል። በክልሉ ህብረት ስራ ኮሚሽን የግብዓትና ግብይት ዳይሬክተር አቶ ዓለምዘውድ ስሜነህ በበኩላቸው፤ ወደ መጋዝኖች የደረሰውን ማዳበሪያ በወቅቱ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። ወደ ዩኒየኖች መጋዝኖች የደረሰውን ማዳበሪያ ወደ መሰረታዊ ህብረት ስራ ማህበራት በማጓጓዝ ፈጥኖ ለአርሶ አደሩ የማሰራጨት ስራ እየተሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ለመጪው መኸር 841 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለማሰራጨት ግብ ይዞ እየሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን የአድማስ ዩኒየን ስራ አስኪያጅ አቶ መሰረት ወርቄ ናቸው። በመጋዘን ያለውን ጨምሮ እስካሁን በዞኑ 526 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ቀድመው ለሚዘሩ ሰብሎች ለማሰራጨት እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ባለፈው ዓመት ወደ ክልሉ ከገባው 7 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ከ7 ሚሊዮን ኩንታል የሚልቀው ጥቅም ላይ እንደዋለም ተገልጿል።
በዞኑ እየተከናወኑ የሚገኙ የመንገድ መሰረተ ልማቶች የማህበረሰቡን ችግር በተጨባጭ የሚቀይሩ ናቸው
Mar 15, 2026 107
፤ መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፦ በኢሉአባቦር ዞን በተያዘው ዓመት እየተከናወኑ የሚገኙ የመንገድ መሰረተ ልማቶች በክረምትም ሆነ በበጋ አገልግሎት የሚሰጡና የማህበረሰቡን ማህበራዊ ችግር በተጨባጭ የሚቀይሩ መሆናቸውን የዞኑ መንገድና ሎጂስቲክስ ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በግብርናው ዘርፍ የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመረው ጥረት ውጤት እየተመዘገበበት ነው የኢሉአባቦር ዞን መንገድና ሎጂስቲክስ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጣሰው አሰፋ እንደገለፁት፤ በዞኑ ወደ 250 ኪሎ ሜትር የሚጠጋ የመስመር ዝርጋታና የነባር መስመሮች ጥገናን ጨምሮ የ4 አዳዲስ ድልድዮች ግንባታ እየተከናወነ ነው። የመንገድ መሰረተ ልማት ግንባታው ወረዳን ከወረዳ እንዲሁም በወረዳ ውስጥ ለውስጥ ቀበሌን ከቀበሌ የሚያገናኙ የአዳዲስ መስመሮች ዝርጋታና ነባር መስመሮች ጥገናና ደረጃ ማሳደግን ታሳቢ ባደረገ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ በወረዳዎች ውስጥ ለውስጥ ቀበሌን ከቀበሌ የሚያገናኙ 16 የመንገድ ግንባታን ጨምሮ ከ32 ኪሎ ሜትር በላይ የአዳዲስ መንገዶች ስራ እየተከናወነ መሆኑንም አመልክተዋል። እንዲሁም የነባር መንገዶች የጥገናና ደረጃ ማሻሻል ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመው የ4 አዳዲስ ድልድዮች ግንባታም እየተከናወነ ስለመሆኑም አክለዋል። ከለውጡ ወዲህ በዞኑ በተለይ ለገጠር መንገዶች ተደራሽነት በተሰጠው ትኩረት ወረዳን ከወረዳና ቀበሌንም ከቀበሌ የሚያገናኙ የ45 መንገዶች ግንባታ ተከናውኗል ብለዋል። በዞኑ በተያዘው ዓመት እየተከናወኑ የሚገኙ የመንገድ መሰረተ ልማቶች በክረምትም ሆነ በበጋ አገልግሎት የሚሰጡና የማህበረሰቡን ማህበራዊ ችግር በተጨባጭ የሚቀይሩ መሆናቸውንም ኃላፊው አመልክተዋል። በዞኑ የአሌ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አቶ ያደታ ዲሳሳና አቶ ግርማ አባተ፤ በተለይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በመንገድ ዝርጋታና ደረጃ ማሳደግ የተሰሩ ስራዎች ከአጎራባች ወረዳ ቀበሌዎች ጋር ያላቸው ግንኙነት እንዲጠናከር ማድረጉን ገልጸዋል። መንገዶቹ በክረምትም ሆነ በበጋ አገልግሎት ስለሚሰጡ የማህበራዊ ግንኙነት መጠናከር ብቻም ሳይሆን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንዳሳደገላቸው ነዋሪዎቹ ተናግረዋል። ነዋሪዎቹ አክለውም በተለይ በኦኖኑ ቀበሌ በጉመሮ ወንዝ ላይ የተገነባው ድልድይ የዘመናት የሕዝብ ጥያቄን የመለሰ ብቻ ሳይሆን በአካባቢው በወንዝ ሙላት ምክንያት ይጠፋ የነበረን የሰው ህይወት የታደገ ነው ብለዋል። በአካባቢያቸው የተገነቡት መንገዶችና ድልድዮች የቀደሙ ችግሮቻቸውን የቀረፉላቸውና ተጠቃሚነታቸው እንዲጨምር እያደረጉ እንደሚገኙ የገለፁት ደግሞ በዞኑ የዲዱ ወረዳ ነዋሪዎቹ አቶ ደሳለኝ ደጋጋ እና ወይዘሮ ደመቀች ረጋሳ ናቸው። በተለይ በዲቦ ወንዝ ላይ የተገነባው ድልድይ በዕለት ተዕለት እንቅስቃሴዎቻቸው ላይ የነበረውን ተፅዕኖ እንደቀረፈላቸውም አንስተዋል።
በብሄረሰብ አስተዳደሩ ለመኽር እርሻ የሚውል በቂ የአፈር ማዳበሪያ ቀርቧል
Mar 15, 2026 84
ሰቆጣ ፤ መጋቢት 6 /2018 (ኢዜአ)፦በዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር ለ2018/19 የምርት ዘመን የሚውል በቂ የአፈር ማዳበሪያ ወቅቱን ጠብቆ መቅረብ መቻሉን የብሄረሰብ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በክልሉ የህዝቡን የመልማት ጥያቄዎች ለመመለስ በተሰራው ስራ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ነው የመምሪያው ኃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በመኸርና በመስኖ የሚካሄደውን የሰብል ልማት ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ስራወዎች እየተሰሩ ነው። በዚህም በ2018/19 የምርት ዘመን የሚካሄደውን የሰብል ልማት ምርታማነት ለማሳደግ 40ሺህ ኩንታል ማዳበሪያ ለማስገባት ታቅዶ እንቅስቃሴዎች እየተካሄዱ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በተደረገ ጥረትም ካለፈው ዓመት የተረፈውን ጨምሮ አዲስ የገባ ከ33ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ወደ ብሄረሰብ አስተዳደሩ ደርሶ እየተሰራጨ መሆኑን ተናግረዋል። የገባው ማዳበሪያ በዋቢ ዩኒየንና በህብረት ስራ ማህበራት በኩል እየተሰራጨ እንደሚገኝ ጠቁመው ቀሪውን ለማስገባት ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የአፈር ማዳበሪያ ቀድሞ መድረሱ አርሶ አደሩ በወቅቱ በመዝራትና በመንከባከብ የሚጠበቀውን ምርት ለማምረት የሚያስችል መሆኑን ገልፀዋል። የዋቢ ሁለገብ የገበሬዎች ህብረት ስራ ዩኒየን የግብይት ባለሙያ አቶ ተስፋዬ ታረቀ በበኩላቸው፤ የአፈር ማዳበሪያው በዩኒየኑ መጋዘኖች ተከዝኖ ወደ ወረዳዎች እየተጓጓዘ ነው። ወደ ወረዳዎች የሚላከው የአፈር ማዳበሪያም በቀበሌ ህብረት ስራ ማህበራት በኩል ለአርሶ አደሩ ተደራሽ እየሆነ ነው ብለዋል። በሰቆጣ ወረዳ 01 ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ማሞ አለሙ እንዳሉት የአፈር ማዳበሪያው በወቅቱ መቅረብ መቻሉ ለአርሶ አደሩ ፈጥኖ የእርሻ ስራውን እንዲያከናውን የሚያስችል ነው። ለግማሽ ሄክታር የእርሻ መሬታቸው የአፈር ማዳበሪያ ቀድመው በመግዛት በወቅቱ ሰብላቸውን እንደሚዘሩም ተናግረዋል። በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን በዘንድሮው ዓመት 120ሺህ 638 ሄክታር መሬት በሰብል ለመሸፈን ተቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል።
በመዲናዋ በህገ ወጥ የነዳጅ ግብይት የተሰማሩ አካላት ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናከሮ ይቀጥላል
Mar 14, 2026 310
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2018(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ በህገ ወጥ የነዳጅ ግብይት በተሰማሩ አካላት ላይ የሚወሰደው ሕጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ ተጠናከሮ እንደሚቀጥል የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ እና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ ገለጹ። የአስተዳደሩ ንግድ ቢሮ ከነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣን ጋር በመተባበር በከተማዋ ከነዳጅ ግብይት ጋር ተያይዞ የሚስተዋሉ ማነቆዎችን ለመቅረፍ ከዘርፉ ተዋናዮች ጋር ውይይት አካሂዷል። በዚሁ ወቅት የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ፤ የኢትዮጵያን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ለማሳለጥ የነዳጅ ምርት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። ለዚህም መንግስት የነዳጅ ምርትን በከፍተኛ የገንዘብ ድጎማ ለተጠቃሚው ማህበረሰብ እንዲሰራጭ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ሆኖም አንድ አንድ ማደያዎችና አከፋፋይ ኩባንያዎች የነዳጅ ምርትን በሕጋዊ ሥርዓት እንዳይሰራጭ በማድረግ ሕገ-ወጥ ተግባር እንደሚፈጽሙ አንስተዋል። በአዲስ አበባም በቂ የነዳጅ ክምችት እያለ ከአሰራር ውጪ ደንበኞችን በማጉላላት ሕገ-ወጥ ተግባር የሚፈጽሙ አካላት መኖራቸውን አስረድተዋል። በቀጣይም የባለድርሻ አካላትን ተሳትፎ በማጠናከር የአሰራር ጥሰት የሚፈጽሙ አካላት ላይ ጠንካራ ሕጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ እንደሚወሰድ አሳስበዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ ኃላፊ ሀቢባ ሲራጅ በበኩላቸው፤ በነዳጅ የምርት ሥርጭት ወቅት ሕገ-ወጥ የግብይት ድርጊቶች እንደሚስተዋሉ በተደረገ ክትትልና ቁጥጥር ተረጋግጧል ብለዋል። መድረኩ በነዳጅ ምርት ሥርጭት ወቅት ከተቀመጠው ሕጋዊ የአሰራር ውጪ ሕገ-ወጥ ግብይት የሚፈጽሙ ማደያዎችንና ኩባንያዎችን ለማረም ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው አስረድተዋል። በቀጣይም በግብይቱ ላይ የሚስተዋሉ ሕገ-ወጥነቶችን በማረም የሚወሰደው ሕግና ሥርዓትን የማስከበር ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል። የነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ደስታው መኳንንት (ዶ/ር)፤ መንግስት በከፍተኛ የገንዘብ ድጎማ ወደሀገር ቤት የሚያስገባውን የነዳጅ ምርት በሕጋዊ ሥረዓት ማሰራጨት ያስፈልጋል ብለዋል። የነዳጅ ምርት የሚያሰራጩ ማደያዎችና አከፋፋዮችም በተቀመጡ የአሰራር ሥርዓት መሠረት ለተጠቃሚው ማዳረስ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል አስራት ዴኔሮ በበኩላቸው፤ በነዳጅ ምርት ሥርጭት ላይ የሚስተዋሉ ሕገ-ወጥነቶች ለማረም ጠንካራ እምርጃ ይወሰዳል ብለዋል። ባለድርሻ አካላትም በወሰዱት ኃላፊነት መሰረት የነዳጅ ምርትን ሕጋዊ የአሰራር ሥርዓት ተከትለው ማሰራጨትና ማከፋፈል እንዳለባቸው አሳስበዋል።
በክልሉ የህዝቡን የመልማት ጥያቄዎች ለመመለስ በተሰራው ስራ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ነው
Mar 14, 2026 94
ወላይታ ሶዶ፤ መጋቢት 5/2018(ኢዜአ):- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የህዝቡን የመልማት ጥያቄዎች ለመመለስ በተሰራው ስራ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ ተናገሩ። በክልሉ የወላይታ ዞን ዳሞት ሶሬ ወረዳ፣ በመንግሥትና በግል ባለሀብቶች ቅንጅት ከ125 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆኑ። ለአገልግሎት ከበቁት ፕሮጀክቶች መካከል የንፁህ መጠጥ ውሃ፣ የመንገድና የድልድይ እንዲሁም የጤና ተቋማት መሆናቸው ተገልጿል። በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የክልሉ መንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ እንደገለጹት፤ መንግሥት ከግሉ ዘርፍ ጋር በቅንጅት በመሥራቱ በክልሉ የሕዝቡ የመልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ እያገኙ ነው። "ሕዝቡንና የግሉን ዘርፍ በማሳተፍ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ከግብ እንዲደርሱና ሁለንተናዊ እድገት እንዲረጋገጥ በትብብር መሥራት ይገባል" ሲሉም አሳስበዋል። በአጠቃላይ ባለፉት ዓመታት በክልሉ የህዝቡን የመልማት ጥያቄዎች ለመመለስ በተሰራው ስራ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን አስረድተዋል። የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ሳሙኤል ተሰማ (ረዳት ፕሮፌሰር) በበኩላቸው፣ የሕዝቡን የመሠረተ ልማት ችግሮች ለመፍታት በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ በበጀት ዓመቱ ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት ከበቁት መካከል የተለያዩ ቀበሌዎችን የሚያገናኝ ከ86 ኪሎ ሜትር በላይ የጠጠር መንገድና 8 ድልድዮች ይገኙበታል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም 32 ተጨማሪ ፕሮጀክቶች በገንባታ ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል። የሕክምና ግብዓት ችግርን ለመቅረፍ ከ384 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መድኃኒቶችና መሣሪያዎች መቅረባቸውን አንስተው ከተገነቡ 21 ሞዴል የማኅበረሰብ መድኃኒት ቤቶች መካከል 12ቱ ሙሉ በሙሉ አገልግሎት ጀምረዋል ብለዋል። በዳሞት ሶሬ ወረዳ የተመረቀው የንጹሕ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት በ6 ቀበሌዎች የሚኖሩ ከ20 ሺህ በላይ አባወራዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች የሆኑት አቶ አስራት አበበ እና ወይዘሮ ዘማች ሰለሞን፣ ለረጅም ጊዜ የሕዝብ ጥያቄ ሆነው የቆዩ የድልድይና የመድኃኒት ቤት ግንባታዎች ተጠናቅቀው ለአገልግሎት በመብቃታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። መሰረተ ልማቶቹ ምርታቸውን ወደ ገበያ ለማውጣትና የተሻለ የጤና አገልግሎት ለማግኘት ትልቅ እገዛ እንደሚያደርጉላቸውም ጠቁመዋል። የሥራ ኃላፊዎቹ ሕብረተሰቡ ለአገልግሎት በቁ የልማት ፕሮጀክቶችን እንደራሱ ንብረት በመቁጠር በባለቤትነት እንዲጠብቃቸው ጥሪ አቅርበዋል።
ሰላምን ከማጽናት ጎን ለጎን የወጣቱን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው- የባህርዳር ከተማ አስተዳደር
Mar 14, 2026 82
ባህርዳር፤ መጋቢት 5/2018(ኢዜአ)፡-ሰላምን ከማጽናት ጎን ለጎን የተጠናከረ የልማት ስራ በመስራት የወጣቱን ተሳትፎና ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው ገለፁ። የባህርዳር ከተማ አስተዳደር የስራ ዕድል ተጠቃሚ ከሆኑ ወጣቶች ጋር በወቅታዊ ጉዳይ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ እያካሔደ ነው። የአስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ የሀገር አንድነትና ብልፅግናን በማረጋገጥ ጠንካራ ሃገር መገንባት የሚቻለው ወጣቱን ትውልድ በንቃት በማሳተፍና ዘላቂ ተጠቃሚነቱን ማረጋገጥ ሲቻል ነው። በአሁኑ ወቅትም ወጣቱ ትውልድን የሰላምና የልማት ዋና አቅም አድርጎ በመሰራቱ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን እንደተቻለም ነው የገለጹት። ከተማ አስተዳደሩም በኮሪደርና ሌሎች ሰፋፊ የልማት ፕሮጀክቶች ትግበራና በተለያዩ የሙያ መስኮች ወጣቱ የስራ እድል እንዲያገኝና የልማት አርበኝነቱን እንዲያረጋግጥ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። ይሕንኑ ተሞክሮ በማስፋትም የስራ ዕድል ተጠቃሚ ያልሆኑ ወጣቶችን በማደራጀት፣ በማሰልጠን፣የብድርና የመስሪያ ቦታ ድጋፎችን በማድረግ ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉን ጠቅሰዋል። የከተማ የአስተዳደሩ ስራና ስልጠና መምሪያ ኃላፊ አቶ ዘመነ አሰፋ በዚሁ ወቅት ባቀረቡት ጽሁፍ እንደገለጹት፤ በከተማዋ በበጀት ዓመቱ ለ45 ሺህ 349 ወጣቶች የስራ ዕድል ለመፍጠር ግብ ተይዞ እየተሰራ ይገኛል። ባለፉት 8 ወራትም በግብርና፤ በማኑፋክቸሪንግ፣ በኮንስትራክሽን፣ በኮሪደር ልማትና ሌሎች ዘርፎች ለ38 ሺህ 546 ወጣቶች የስራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉን ገልፀዋል። የአማራ ክልል ወጣቶች ማህበር ፕሬዝዳንት ወጣት ጋሻው አዘነ በበኩሉ፤ ስላምን አፅንቶ በማዝለቅና ልማቱን በማፋጠን አገራችን ወደ ብልጽግና ማማ ለማሸጋገር የወጣቱ ሚና የላቀ መሆኑን ነው የሚናገረው። የወጣቱን ተጠቃሚነት በዘላቂነት ማረጋገጥ የሚቻለው በየደረጃው ሰላምን ማስፈን ሲቻል መሆኑን በመገንዘብም ወጣቱ ሰላምን ለማጽናት ተግቶ አንደሚሰራ ነው ያመለከተው። የመድረኩ ተሳታፊ ነፃነት አጠቃ በበኩሏ ያለ ሰላም ሰርቶ መለወጥም ለአገር እድገት ማምጣት የማይታሰብ በመሆኑ የተገኝውን ሰላም ለማጽናት በትኩረት እንሰራለን ነው የምትለው። በውይይት መድረኩ ላይም ከሁሉም ክፍለ ከተሞችና ቀበሌዎች የተውጣጡ ወጣቶችና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ተሳትፈዋል።
በሸገር ከተማ ባለፉት ስምንት ወራት 25 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር ገቢ ተሰበሰበ
Mar 14, 2026 88
ሸገር፤ መጋቢት 5/2018(ኢዜአ)፦ በሸገር ከተማ ግብርን በቴክኖሎጂ ታግዞ በመሰብሰብና የተሻሻሉ የታክስ ህጎችን በመተግበር ባለፉት ስምንት ወራት 25 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡን የከተማው ገቢዎች ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የሸገር ከተማ ገቢዎች ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ መልካሙ አምባው ለኢዜአ እንደተናገሩት በከተማው የሚሰበሰብ ገቢን ለማሳደግ ከባለድርሻ አካላት ጋር የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። ሸገር ከተማ ከመቋቋሙ በፊት ሲሰበሰብ የነበረው ገቢ ከ5 ቢለየን ብር በታች እንደነበርና የከተማው መቋቋምን ተከትሎ የገቢው መጠን እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት ከከተማው 24 በሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡን አስታውሰው በተያዘው ዓመትም 39 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱንና ባለፉት ስምንት ወራት ብቻ 25 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር መሰብሰቡን አስታውቀዋል። ገቢው ከማዘጋጃ ቤታዊ፣ ቀጥተኛና ቀጥተኛ ካልሆኑ የገቢ አርዕስቶች የተሰበሰበ መሆኑን ጠቁመው፣ ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ብልጫ እንዳለውም ተናግረዋል። የግብር አሰባሰብ ሥራው በቴክኖሎጂ መደገፉ፣ የተሻሻሉ የታክስ ህጎች ተግባራዊ መደረጋቸውና የአገልግሎት አሰጣጡ መዘመኑ ዘንድሮ ከፍተኛ ገቢ እንዲሰበሰብ አስችሏል ብለዋል። የህብረተሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ ላይ የተሰጠው ትኩረት፣ የግብር ከፋዮች ቁጥር መጨመርና የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ አሰራር ማደግ ለገቢው መጨመር ከፍተኛ እገዛ አድርጓል ነው ያሉት። በዘርፉ ህገ-ውጥ ተግባራትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በተደረገ እንቅስቃሴ ለሸጡት እቃ ደረሰኝ ሳይቆርጡ የተገኙ 59 ግብር ከፋይ ነጋዴዎች በገንዘብ መቀጣታቸውን አንስተዋል። ህግ ተላልፈው በተገኙ 33 የተቋሙ ሠራተኞች ላይም አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን ጠቁመው ተግባሩ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።