ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በምዕራብ ሸዋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል
Jul 30, 2026 46
አምቦ ፤ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ):- በምዕራብ ሸዋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በዞኑ አደአ በርጋ ወረዳ ግንባታቸው የተጠናቀቁ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ተደርገዋል፡፡ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ በምረቃ ስርዓቱ ላይ እንደገለጹት፣ በዞኑ በርካታ የልማት ስራዎችን በማከናወን የህዝቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው።   በ2018 በጀት ዓመት ከ5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ በሚሆን ወጪ በዞኑ በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች የተገነቡ 585 ፕሮጀክቶች ተጠናቀቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን በማሳያነት አንስተዋል። "የማንጨርሰውን ፕሮጀክት አንጀምርም" ብለን ለህዝባችን ቃል በገባነው መሰረት ሁሉንም ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በማብቃታችን ታላቅ ደስታ ይሰማናል በማለትም ተናግረዋል፡፡ በዞኑ የአደኣ በርጋ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ከበደ በቀለ በበኩላቸው፤ በወረዳው በመንግሥት በጀትና በሕብረተሰቡ ተሳትፎ ከ 274 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 33 የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን አስታውቀዋል።   ዛሬ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ከሆኑት ፕሮጀክቶች መካከል፣ የቅድመ መደበኛና አንጀኛ ደረጃ "ኦልማ አዳ" ትምህርት በቶች፣ ሞዴል የህዝብ መድሃኒት ቤት፣ የከብቶች ማድለቢያና ለዶሮ እርባታ የሚሆኑ ሼዶች እና የኢንጭኒ ከተማ ኮሪደር ልማት ይገኙበታል ብለዋል። ፕሮጀክቶቹ የሕዝቡን የልማት ጥያቄ ከመመለስና የመልካም አስተዳደር ችግርን ከመፍታት ባለፈ ለዜጎች የስራ እድል እንደፈጠሩላቸውም ገልጸዋል። በወረዳው ባለፉት ጥቂት ዓመታት የሰላም እጦት ችግር እንደነበረና አሁን ላይ ህብረተሰቡ ከመንግሥት ፀጥታ ሃይሎች ጋር ተቀናጅቶ በመስራት በተገኘው ሰላም የህዝቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ የሚችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን ለአገልግሎት ማብቃት መቻሉን ጠቁመዋል። በምረቃው ላይ የተገኙት የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው የልማት ፕሮጀክቶቹ ግንባታ የረጅም ጊዜ ጥያቄያቸው መልስ ያገኘበት በመሆኑ መደሰታቸውን በመግለጽ፤ አሁን ያገኙትን ሰላም በማፅናት የተመረቁ ፕሮጀክቶችን እየተንከባከቡ ለመጪው ትውልድ እደሚያሳልፉ ተናግረዋል።   ከአከባቢው ነዋሪዎች መካከል አባ ገዳ ግርማ ዱጉማ፤ ፕሮጀክቶቹ የረጂም ጊዜ ጥያቄያቸው የተመለሰበት ስለሆነ ጠብቀው ለተተኪው ትውልድ ለማስተላለፍ ሃላፊነታቸውን የሚወጡ መሆኑን ገልጸዋል።   ሌላው የወረዳው ነዋሪ ወይዘሮ ተዋበች በቀለ በበኩላቸው በአካባቢያቸው የተሰራው ሞዴል የህዝብ መድሃኒት ቤት የነበረባቸውን የጤና አገልግሎት ችግር ለመፍታት የሚያስችል በመሆኑ ደስታቸውን ገልጸዋል።
በጅማ ዞን የተገነቡ ፕሮጀክቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ አድርገዋል
Jul 30, 2026 179
ጅማ፤ ሀምሌ 23/2018 (ኢዜአ) ፡-በጅማ ዞን በመንግስትና በህዝብ ተሳትፎ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ ማድረጋቸውን የጅማ ዞን አስተዳዳሪ ቲጃኒ ናስር ገለጹ።   በጅማ ዞን ሰቃ ጨቆርሳ ወረዳ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። ከፕሮጀክቶቹ መካከል የግብርና ግብዓት ማከማቻ፣ የመንገድ፣ ድልድይ ፣የሁለተኛ ትውልድ የጤና ኬላ፣ የገበያ ማዕከል እና የወረዳው አስተዳደር ህንፃን ጨምሮ ሌሎችም ይገኙበታል።   የጅማ ዞን አስተዳዳሪ ቲጃኒ ናስር በወቅቱ እንዳሉት የህብረተሰቡን የመሠረተ ልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ፕሮጀክቶች በፍጥነትና በጥራት ተገንብተው እንዲጠናቀቁ እየተደረገ ነው ። በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በመንግስት እና በህዝብ ተሳትፎ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ አድርገዋል ብለዋል ። በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት አመት በ5 ነጥብ 1 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ ከ1 ሺህ 876 በላይ ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን ተናግረዋል ።   ፕሮጀክቶቹ ለህዝብ ለጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የሰቃ ጨቆርሳ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አብዱልከሪም አባራያ በበኩላቸው በወረዳው በበጀት ዓመቱ ከ800 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ግንባታቸው ከተጀመሩ 33 ፕሮጀክቶች ውስጥ 23ቱ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ተደርገዋል ብለዋል። ቀሪዎቹም በአጭር ጊዜ ውስጥ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚደረጉ አመላክተዋል ። የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ እየተደረገ ያለው የመሠረተ ልማት ግንባታ የሚበረታታ ነው ያሉት ደግሞ በጅማ ዞን ሰቃ ጨቆርሳ ወረዳ ነዋሪ አቶ መሀመድ ዘይን ተማም ናቸው።   አቶ አበዱላሂ አባ ጀበል በበኩላቸው በወረዳው ዶዩ ቃጨማ ቀበሌ የተገነባው የግብዓት ማቆያ እና ማከማቻ ከዚህ ቀደም የግብርና ግብአቶችን ለማግኘት ወደ አጎራባች ወረዳዎች በመጓዝ የሚባክንን ግዜና ገንዘብ እንደቆጠበላቸው ተናግረዋል።  
በ2018 በጀት ዓመት በመንግሥት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ከ597 ቢሊየን ብር በላይ ግዥ ተፈጽሟል
Jul 30, 2026 280
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በመንግሥት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ከ597 ቢሊየን ብር በላይ የተጠናቀቀ ግዥ መፈጸሙን የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ገለጸ። ባለሥልጣኑ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት ግዥና ንብረት አስተዳደር አፈጻጸምና የ2019 ዕቅድ ላይ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ጋር ምክክር እያደረገ ይገኛል። በመርሃ ግብሩ የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴን ጨምሮ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶችና የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።   የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር መሰረት መስቀሌ በዚህ ወቅት፤ ባለሥልጣኑ የመንግሥት ግዥ ሥርዓትን፣ የንብረት አስተዳደርንና አወጋገድ ሂደትን በኤሌክትሮኒክ ሥርዓት በማስተዳደር ለዲጂታል ኢትዮጵያ ሽግግር ገንቢ ሚና እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል። በ2018 በጀት ዓመት 172 የፌዴራል መሥሪያ ቤቶችና 196 ቅርንጫፍ ተቋማቶቻቸው የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትን መጠቀማቸውን ገልጸዋል። በዚህ ሥርዓት ተመዝግበው ምርትና አገልግሎት የሚያቀርቡ ተቋማት ቁጥርም ከ135 ሺህ በላይ መድረሱን ጠቁመዋል። የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓቱ በየጊዜው ማሻሻያ እየተደረገለት ለአጠቃቀም ምቹ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነትን የሚያሰፍን እየሆነ መምጣቱንም ተናግረዋል። በዚህም በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት በመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ከ597 ቢሊየን ብር በላይ ግዥ መፈጸሙን አስታውቀዋል።   የግዥ ሥርዓቱ ከፌዴራል ተቋማት ባለፈ በኦሮሚያ ክልልና በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተግባራዊ መደረጉን አስረድተዋል። በሌሎች ክልሎችም የሥርዓቱን መሠረተ ልማት ለማስፋፋት በስልጠናና በአቅም ግንባታ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። ባለሥልጣኑ ከኤሌክትሮኒክ ግዥ ባሻገር የተሽከርካሪዎችን እንቅስቃሴና የነዳጅ አጠቃቀም መቆጣጠር የሚያስችል ''e-Fleet Management'' ሥርዓት ወደ ሥራ ማስገባቱንም ገልጸዋል። በዚህም 139 ተቋማት ሥርዓቱን ለመጠቀም መግባታቸውንና 69 ተቋማት ከ7 ሺህ በላይ ተሽከርካሪዎችን መረጃ መመዝገባቸውን ጠቁመዋል። በ2019 በጀት ዓመትም ሁሉም ባለበጀት መሥሪያ ቤቶች ወደ ሥርዓቱ እንዲገቡ ክትትል እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። በ2018 በጀት ዓመት የተመዘገቡ ውጤቶች የአገልግሎት አሰጣጡን ማቀላጠፍና የቁጥጥር ሥርዓቱን ማጠናከር የሚያስችል የዲጂታል ሽግግር እየተፈጠረ መሆኑን ያሳያሉ ብለዋል።
በዞኑ የማር ምርት አቅርቦትና ተጠቃሚነት አድጓል
Jul 30, 2026 299
መቱ ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦ በዞኑ የማር ምርት ቴክኖሎጂ፣ አቅርቦትና ተጠቃሚነት ማደጉን የኢሊባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አወል መሐመድ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤ባለፉት አምስት ዓመታት ለማር ምርት በተሰጠው ትኩረት በዘርፉ ለውጥ ለማምጣት ተችሏል።   በዋናነትም ዘመናዊ ቀፎና ለስራው የሚያስፈልጉ ተያያዥ ቴክኖሎጂዎችን በስፋት በማዳረስ ዘርፉን ለማሳደግ በተደረገው ጥረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልፀዋል። ይህን ተከትሎም ከአምስት ዓመታት በፊት በዞኑ ከ5 ሺ ቶን የማይበልጥ የነበረው ዓመታዊ የማር ምርት መጠንን ወደ 20 ሺ ቶን ከፍ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። በመስኩ በቀፎ ማምረት ስራ ተደራጅተው የተሰማሩትን ጨምሮ ለአርሶ አደሮችና በማር ንግድ ለተሰማሩ ዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል መከፈቱንም ተናግረዋል። በዞኑ በቾ ወረዳ ከ8 ሺ በላይ አርሶ አደሮችና ማሕበራት በንብ ማነብና የማር ምርት ተሰማርተው እንደሚገኙ የገለጹት ደግሞ የወረዳው ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ዲቤሳ ናቸው።   ጽህፈት ቤቱ ለዘመናዊ ቀፎ አቅርቦት በሰጠው ትኩረትም ከ50 ሺህ በላይ ቀፎዎችን ለማሕበራትና አርሶ አደሮች ማቅረብ መቻሉን ገልፀዋል። በወረዳው የማር ምርት ልማት ላይ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል ወይዘሮ አይናለም ጌታቸው፤ በ12 ቀፎዎች የጀመሩትን የማር ምርት ወደ ሃምሳ ቀፎ ማሳደጋቸውን ነው የሚናገሩት።   በማር ምርቱ የቤተሰብ ፍጆታን ከመሸፈን ባለፈ በዓመት እስከ ሶስት መቶ ኪሎ ግራም ለገበያ እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል። ወጣት ሻቡ አብዱራህማን እና ጓደኞቹ በበኩላቸው፤ በማሕበር ተደራጅተው በማር ምርት በመሰማራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። በመስኩ ጠንክረው በመስራት ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ የስራ እድል ለመፍጠር ጠንክረው እየሰሩ መሆኑንም ገልጸዋል። በኢሉባቦር ዞን በአጠቃላይ ከ70 ሺ በላይ አርሶ አደሮች በንብ ማነብና በማር ምርት ልማት ተሰማርተዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓት ውጤታማነትን አሻሽሏል
Jul 30, 2026 373
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓትንና የወጪ ውጤታማነትን ማሻሻሉን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገለጹ። የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት ግዥና ንብረት አፈጻጸምና የ2019 ዕቅድን በተመለከተ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶችና የሀብት አስተዳደር ኃላፊዎች ጋር ውይይት አድርጓል።   የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የመንግሥት ግዥና ንብረት አስተዳደር ሥርዓት ለኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለፊስካል መረጋጋት፣ ለመንግሥት ወጪ ቅልጥፍና፣ ለግልጽነትና ተጠያቂነት መጠናከር የጎላ ስትራቴጂካዊ ሚና አለው። የመንግሥት ግዥ የመንግሥት ፖሊሲ ወደ ተግባር የሚቀየርበት፣ የሕዝብ ሀብት በኃላፊነት የሚተዳደርበት፣ የአገልግሎት ጥራትን የሚያሻሽልና ሀገራዊ ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን የሚደግፍ መሆኑን ገልጸዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትንና የወጪ ውጤታማነትን ማሻሻል አስችሏል ብለዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የመንግሥት የኤሌክትሮኒክ ግዥን በማስፋት፣ የግዥ ዝመናን በማጠናከር፣ ሕጎችና አሠራሮችን በማዘመን አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፤ ተቋማዊ አቅምን ከማጠናከር ባለፈ በመንግሥት ወጪ ላይ ግልጽነትና ተጠያቂነትን ያጠናከሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። መንግሥት ለትምህርት፣ ለጤና፣ ለግብርና፣ ለውኃ፣ ለመሠረተ ልማት፣ ለዲጂታል ልማትና መሰል ዘርፎች የሚመድበው በጀት በመንግሥት ግዥ ወደ ተግባር፤ የልማት ፖሊሲ ወደ ውጤት የሚቀየርበት መሆኑንም ተናግረዋል። የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን በኤሌክትሮኒክ ግዥ፣ በዲጂታላይዜሽንና በአሠራር ማሻሻያዎች ያስመዘገባቸው ውጤቶች በመንግሥት ወጪዎች ላይ ያለውን ግልጽነትና ተጠያቂነት የሚያጠናክሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በመንግሥት ግዥ ላይ የሚሻሻለው እያንዳንዱ ሂደት በዜጎች ሕይወት ላይ ተጨባጭ ውጤት የሚያመጣ መሆን አለበት ሲሉም አስገንዝበዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ ግብ የፊስካል ሥርዓትን ማጠናከር፣ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማሳደግና የመንግሥት ወጪን ውጤታማ ማድረግ መሆኑን ገልጸው፤ ለግቡ መሳካት የመንግሥት ግዥ ሥርዓቱን ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተጠያቂነት የሰፈነበት ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። በ2019 በጀት ዓመት ሁሉም የፌዴራል ተቋማት የሚመሩበት መርህ ትክክለኛነት፣ ጥራትና ወቅታዊነት መሆኑን ያነሱት ሚኒስትሩ፣ የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን የዲጂታል ሪፎርም የኢትዮጵያን የዲጂታል ሽግግር ይደግፋል ብለዋል። የዲጂታል ሽግግር አማራጭ ሳይሆን ግዴታ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፣ በበጀት ዓመቱ ሁሉም የፌዴራል ተቋማት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትን በተሟላ ሁኔታ መጠቀም፣ የመንግሥትን ንብረት በዘመናዊ መንገድ ማስተዳደር እንዳለባቸውም ገልጸዋል። የመንግሥት ሀብት የሕዝብ አደራ መሆኑን ገልጸው፤ የሕዝብን አደራ በታማኝነት መጠበቅ የሁሉም የመንግሥት ተቋማት የመጀመሪያ ግዴታ ነው ብለዋል።
በክልሉ በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ ተችሏል 
Jul 30, 2026 308
ባሕር ዳር ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ መቻሉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። የአማራ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 5ተኛ ዓመት የስራ ዘመን 12ኛ መደበኛ ጉባኤ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፤ ለምክር ቤት ባቀረቡት የ2018 በጀት ዓመት የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርት፤ በተለያየ መስክ በተቀናጀና በተናበበ መንገድ በመሰራቱ የተሻለ እድገት ማስመዝገብ አስችሏል ብለዋል። በክልሉ በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተሻለ የኢኮኖሚያዊ እድገት ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸው በተለይም በግብርና፣ በአገልግሎት፣ በኢንዱስትሪ፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም እና ሌሎችም ዘርፎች እመርታዊ እድገት መታየቱን ገልጸዋል። በዚህም የሰብል ምርታማነትን በሄክታር ከ28 ነጥብ 68 በመቶ ወደ 30 ነጥብ 46 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ገልፀዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄም በርካታ ኢንዱስትሪዎችን ወደ ማምረት በማስገባት ተኪ ምርቶችን ከማምረት ባለፈ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በማቅረብ የተሻለ አፈፃፀም ማስመዝገብ መቻሉን አንስተዋል። በማዕድን ዘርፋም ለኮንስትራክሽንና ለኢንዱስትሪ ግብአት የሚሆኑ ምርቶችን ከማምረት ባሻገር ወርቅ፣ ኦፓልና መሰል ማዕድናትን ለገበያ በማቅረብ የውጭ ምንዛሬ ገቢ በማስገኘት አበረታች ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። በክልሉ የሚገኙ ታሪካዊና የተፈጥሮ የቱሪስት የመስህብ ስፍራዎችን በስፋት በማስተዋወቅ ከጎብኝዎች ከ15 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘት እንደተቻለም ጠቅሰዋል። በበጀት ዓመቱ ከ1 ነጥብ 3 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የስራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚ እንዲሆኑ ተደርጓል ብለዋል። በተጨማሪም የገበያ ዋጋ በማረጋጋትና የኑሮ ውድነትን በመከላከል በተሻለ ቅንጅት መሰራቱን አንስተው፤ በዚህም የተመዘገበው እድገት የበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በአጠቃላይ በተከናወኑ ተግባራት የተመዘገቡ ውጤቶች የሚያበረታቱ ቢሆንም አሁንም ከዚህ በተሻለ ትብብር የክልሉን ህዝብ የላቀ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የጨልጨል መስኖ ፕሮጀክትን በፍጥነት አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት እየተሰራ ነው
Jul 30, 2026 485
ሮቤ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦የጨልጨል መስኖ ፕሮጀክትን በጥራትና በፍጥነት አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት እየተሰራ መሆኑን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ገለጸ። የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎችና የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ባሌ እየተገነባ ያለውን የጨልጨል የመስኖ ፕሮጀክት የግንባታ ሂደት ተመልክተዋል። ፕሮጀክቱ በተቋራጭ የአቅም ውስንነትና በዲዛይን ለውጥ ምክንያት ተጓቶ የቆየ ቢሆንም በአሁኑ ወቅት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍና አዲስ ተቋራጭ በመተካት የግንባታ ሥራው እንዲቀጥል ተደርጓል።   በሚኒስቴሩ የመስኖ ፕሮጀክቶች ፕሮግራም ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ አሸናፊ ሊካሳ እንዳሉት፤ የጨልጨል መስኖ ፕሮጀክትን አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት ቀጥተኛ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ነው። በ2012 ዓ.ም የግንባታ ሥራው የተጀመረው የጨልጨል መስኖ ፕሮጀክት በ2018 በጀት ዓመት መጨረሻ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ለማብቃት ታቅዶ እንደነበር አስታውሰዋል።   የመስኖ ፕሮጀክቱ በዲዛይን ችግርና በተቋራጭ የአቅም ውስንነት ምክንያት መጓተቱንም ነው የገለጹት። የመስኖ ፕሮጀክቱ በተለይ በቅድመ-ዕቅዱ በአነስተኛ መስኖ ደረጃ ሊገነባ ታስቦ የነበረ ቢሆንም፣ የልማት አቅሙንና ደረጃውን ከፍ ለማድረግ በተደረገው የዲዛይን ማሻሻያ ምክንያት ግንባታው ለተወሰኑ ጊዜያት ቆሞ እንደነበር አንስተዋል። እንዲሁም ከተቋራጭ የአቅም ውስንነት ጋር ተያይዞ ያገጠመውን ችግር ለመቅረፍ ፤የነበረውን ተቋራጭ ውል በማቋረጥ በዘርፉ ልምድና አቅም ያለው ተቋራጭ ስራውን እንዲቀጥል መደረጉን አመልክተዋል። የጨልጨል መስኖ ፕሮጀክት በሁለት ሎት ተከፋፍሎ እየተገነባ ሲሆን፤ አንደኛው የግድቡ ግንባታ ሁለተኛው ደግሞ የመስኖ ካናል ዝርጋታ መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም 4 ሺህ 145 ሄክታር ማልማት የሚችለው የካናል ሥራ ሙሉ በሙሉ የተጠናቀቀ ሲሆን የተጓተተውን የግድቡን ሥራ በማጠናቀቅ ወደ ሥራ ለማስገባት ትኩረት መደረጉን አክሏል።   የፕሮጀክቱን ግንባታ በአዲስ መልክ እያከናወነ የሚገኘው የአለማየሁ ከተማ ጠቅላላ ሥራ ተቋራጭ ፕሮጀክት ማኔጀር ኢንጂነር ባህሩ ፊኖ በበኩላቸው ፕሮጀክቱን በጥራት ገንብቶ ለማጠናቀቅ በሙሉ አቅም እየሰራን ነው ብለዋል። የፕሮጀክቱ ማነቆ የነበረው የዲዛይን ችግርና የግድቡ መሰረት የሙሌት ማሽን እጥርት ተፈትቶ ቀሪ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። የፕሮጀክቱ አሁናዊ አፈጻጻም 50 በመቶ መጠናቀቁን የገለጹት ኢንጂነር ባህሩ ለግድቡ የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶች በበቂ ሁኔታ በመዘጋጀታቸው በ2019 የበጀት ዓመት ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የጨልጨል መስኖ ፕሮጀክት በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ባሌ ዞን ዝናብ አጠር በሆነው ቆላማ የራይቱ ወረዳ አካባቢ ነው እየተገነባ የሚገኘው። የፕሮጀክቱ ግንባታ ሲጠናቀቅ 4 ሺህ 145 ሔክታር መሬት በማልማት ከስምንት ሺህ በላይ አርሶና አርብቶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ይጠበቃል።
አገልግሎቱ የውጭ ባለሀብቶች በሚሰማሩባቸው የትኛውም የሥራ መስኮች አስተማማኝ የፀጥታና ደኅንነት ምህዳር እንዲፈጠር የሚያግዝ ስምሪት እያከናወነ ይገኛል
Jul 29, 2026 1942
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ)፦ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የውጭ ባለሀብቶች በሚሰማሩባቸው የትኛውም የሥራ መስኮች አስተማማኝ የፀጥታና ደኅንነት ምህዳር እንዲፈጠር የሚያግዝ ስምሪት እያከናወነ እንደሚገኝ የአገልግሎቱ ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) አስታወቁ። የአሜሪካ መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ እና አፍሪካ ምክትል ረዳት ሚኒስትር ማርክ ሚቸል ሀገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ስትራቴጂክ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በትብብር ለመሥራት ያላትን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ በላከው መረጃ እንዳመለከተው፤ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) የአሜሪካ መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ እና አፍሪካ ምክትል ረዳት ሚኒስትር ማርክ ሚቸል ከተመራ ልዑክ ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተዋል። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ ተቋሙ በኢትዮጵያ ለኢንቨስትመንት፣ ለንግድና ለሌሎችም የውጭ ባለሀብቶች ለሚሰማሩባቸው የትኛውም የሥራ መስኮች አስተማማኝ የፀጥታና ደኅንነት ምህዳር እንዲፈጠር የሚያግዝ ስምሪት እያከናወነ ይገኛል፡፡ ይህም ለአሜሪካ የቢዝነስ ማኅበረሰብ መተማመን የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል፡፡   በየጊዜው ሲያጋጥሙ የነበሩ የፀጥታ ስጋቶችን በማስወገድ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ደኅንነትንና ሰላምን የማረጋገጥ ሰፊ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥትም ቀጣናዊ መረጋጋት ለማስፈን የጋራ ተጠቃሚነትን መርህ ያደረጉ ስትራቴጂዎች በመንደፍና ቁርጠኛ አቋም በመያዝ እየተገበረ መሆኑን ገልጸው፤ የመረጃና ደኅንነት ተቋሙም በዚህ በኩል ያለውን ዝግጁነት ጠቁመዋል፡፡ የአሜሪካ መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ እና አፍሪካ ምክትል ረዳት ሚኒስትር ማርክ ሚቸል በበኩላቸው፤ ሀገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ስትራቴጂክ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በትብብር ለመሥራት ያላትን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል፡፡ ረዳት ሚኒስትር ማርክ ሚቸል የአሜሪካ ኩባንያዎች በሀገሪቱ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ተሰማርተው መስራት በሚችሉበት ሁኔታ ላይ ማብራሪያ እንደሰጡና ለዚህም አስቻይ ሁኔታዎች መኖሩን እንደገለፁ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ የላከው መረጃ አመልክቷል።
በክልሉ የሕዝቦችን አብሮነት በማጠናከር የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ይሰራል 
Jul 29, 2026 1304
ሆሳዕና ፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ) :- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሕዝቦችን አብሮነት በማጠናከር የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። በክልሉ የ2018 በጀት ዓመት የፓርቲና የመንግሥት ሥራዎች አፈጻጸም እና የ2019 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ ክልላዊ የከፍተኛ አመራሮች የውይይት መድረክ በሆሳዕና ከተማ ተካሄዷል።   በወቅቱም የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንደገለፁት፤ በክልሉ የሕዝቦችን አብሮነት በማጠናከር የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ይሰራል። ርዕሰ መስተዳድሩ አክለውም፤ የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ተግባራት በተያዘው በጀት ዓመትም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። ለዚህም አመራሩ የጋራ ትርክትን በመገንባትና ሙሉ ጊዜውን ሰጥቶ በመሥራት ለአካባቢው ፈጣን ልማት መረጋገጥ መትጋት እንዳለበት አሳስበዋል። በዋናነትም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የኑሮ ውድነትን በማረጋጋት፣ የሥራ ዕድል በመፍጠርና በሌሎች ኢኮኖሚያዊ መስኮች የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ የተከናወኑ ተግባራት በቀጣይም ልዩ ትኩረት ይሰጣቸዋል ብለዋል። ለሕብረተሰቡ የመልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት እንዲያስችል የገቢ አማራጮችን በማስፋትና ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ መሰብሰብ እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በማረምና ጠንካራ የድጋፍና ክትትል ሥራ በማከናወን ተጨባጭ ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እንደሚሠራም ገልጸዋል።   በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ዲላሞ ኦቶሬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የክልሉ አመራር በፓርቲው መርህ ላይ ተመስርቶ ማኅበረሰቡን ማገልገል እንዳለበት ተናግረዋል። የተረጋጋ የፖለቲካ ምህዳር ከመፍጠር ባለፈ የማኅበረሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጡ ተግባራት ላይ ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንደሚገባም ገልጸዋል። ማኅበረሰቡን ያሳተፉ የንቅናቄ ተግባራትን በማከናወን እየተመዘገቡ የሚገኙ ስኬቶችን ማጠናከር እንደሚጠበቅም ኃላፊው አመልክተዋል።
በክልሉ በግብርና ልማትና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ የተገኙ ስኬቶችን ለማስቀጠል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው
Jul 29, 2026 1341
ሀረር፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ) :- በሐረሪ ክልል በግብርና ልማትና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ የተገኙ ስኬቶችን ለማስቀጠል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ሃላፊ ሮዛ ኡመር ተናገሩ። በክልሉ የ2018 የግብርና ልማት እቅድ አፈጻጸምና የ2019 የግብርና ልማት መሪ እቅድ ላይ የውይይት መድረክ ተካሂዷል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ሃላፊ ሮዛ ኡመር፤ በክልሉ ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት የመውጣት ጥረት ተጨባጭ ውጤቶች እየተመዘገቡበት መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በገጠር ወረዳዎች በመስኖ ልማት የተከናወኑ የልማት ስራዎች ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በቤተሰብ ደረጃ ጭምር የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ ያስቻሉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር በተለይም የእንስሳት ተዋጽኦ እንዲሁም የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ትልቅ እመርታ የተገኘበት ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም ከተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ባሻገር የምግብ ዋስትና መሰረት መሆኑን አንስተው በተያዘው በጀት ዓመትም በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን ተናግረዋል። በግብርና ልማትና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ የተገኙ ስኬቶችን ለማስቀጠል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አንስተው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። የቢሮው የእቅድና ክትትል ዳይሬክተር ሚልኬሳ አህመድ፤ በበጀት ዓመቱ ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሰፋፊ ስራዎች ተከናውነዋል ውጤትም አስገኝተዋል ብለዋል።   በግብርና ዘርፍ በሰብል ልማት፣ የአትክልት እና ፍራፍሬ ምርታማነት እንዲሁም የሌማት ትሩፋት ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን ጠቅሰዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል የግብርና ባለሙያው መሳይ ስለሺ፤ በክልሉ የአርሶ አደሩ ምርታማነትና ተጠቃሚነት ከፍተኛ መሻሻል ማሳየቱን አንስተዋል። በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና እንክብካቤ እንዲሁም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እመርታዊ ለውጥ እያስገኙ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በመድረኩ በ2018 በጀት ዓመት በግብርና ልማት ተግባራት አበረታች ስራ ላከናወኑ የወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት፣ የግብርና ባለሙያዎችና ሌሎች አካላት እውቅና ተሰጥቷል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በመኸር እርሻ እስካሁን ከ385 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Jul 29, 2026 1363
ደብረ ማርቆስ ፤ሃምሌ 22/2018(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን በመኽር ወቅቱ እስከሁን ከ385 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ስብሎች ዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ እምቢአለ አለኽኝ ለኢዜአ እንደገለጹት በያዝነው የመኸር ወቅት ከእለት ፍጆታ ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት በትኩረት እየተሰራ ነው። በምርት ወቅቱ ከ669 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት 26 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል። እስካሁን በተደረገ ጥረት ከ385 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ታርሶ በዘር መሸፈኑን ተናግረዋል ። በቆሎ፣ ገብስ፣ ስንዴ፣ ባቄላ፣ በሎቄ፣ ማሽላ፣ የቢራ ገብስ፣ ጤፍና ሌሎች ገበያ ተኮር ሰብሎች መዘራታቸውን ጠቅሰዋል። በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥም ከ90 በመቶ በላይ የሚሆነውን በመስመር እንዲሁም ከ229 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው ደግሞ በኩታገጠም የተዘራ መሆኑን አብራርተዋል። ምርታማነትን ለማሳደግ በተደረገ ጥረትም ከ660 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ መዋሉን ተናግረዋል። የመኸር እርሻው ከ390 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ እየተካሄደ መሆኑን አስታውቀዋል። በዞኑ የጎዛምን ወረዳ የሸበልማ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አንሙት የሻንበል እንደገለጹት የክረምቱን ዝናብ በመጠቀም ከአንድ ሄክታር በላይ መሬታቸውን በበቆሎና በስንዴ ሰብል መሸፈናቸውን ገልጸዋል። ምርታማነታቸውን ለማሳደግም የግብርና ባለሙያን ምክረ ሃሳብ በመከተል ማዳበሪያ በመጠቀም፣ በኩታ ገጠምና በመስመር መዝራታቸውን አስረድተዋል። የቀበሌው ነዋሪ አርሶአደር ይበልጣል ካሴ በበኩላቸው ባቄላ፣ ገብስና በቆሎ ሰብሎችን ቀድመው መዝራታቸውን ጠቁመው ጤፍ ለመዝራት በዝግጅት ላይ መሆናቸውን አስረድተዋል።  
በክልሉ 51 የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታን በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ማድረግ ተችሏል
Jul 29, 2026 1326
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ):-በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 51 የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታቸው ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የመስኖ ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ አየልኝ መሳፍንት ለኢዜአ እንዳሉት፤ በክልሉ ዘመናዊ የመስኖ አውታሮችን ግንባታ በማስፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት እየተሰራ ይገኛል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም አርሶ አደሩን ከባህላዊ አሰራር በማላቀቅ በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ ማምረት የሚችልበትን እድል ከማስፋት አንፃር የተሻለ ስራ ማከናወን ተችሏል ነው ያሉት። ለመስኖ ልማት የሚውሉ አካባቢዎችን በጥናት ከመለየት ባለፈ ወደ ግንባታ በማስገባት አርሶ አደሩ የዘመናዊ መስኖ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆን ማድረግ መቻሉንም አብራርተዋል። በተቀናጀ መንገድ በተደረገ ጥረትም 90 የመስኖ ፕሮጀክቶችን ወደ ግንባታ ማስገባት መቻሉን ጠቅሰው፤ ከእነዚህ ውስጥ 51 የሚሆኑትን በማጠናቀቅ ለልማት ስራ እንዲውሉ ለማድረግ ተችሏል ነው ያሉት። ግንባታቸው የተጠናቀቁ የመስኖ ፕሮጀክቶችም ከ3 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት ማልማት ያስቻሉ ሲሆን ከ 7 ሺህ 500 በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሆኑም ገልፀዋል። በተጨማሪም ከ30 ሺህ ሄከታር በላይ መሬት ማልማት የሚችሉ 99 የመስኖ ፕሮጀክቶች ጥናትና ዲዛይንን በማጠናቀቅ ለግንባታ ስራ ዝግጁ ማድረግ እንደተቻለ ተናግረዋል። የመስኖ አውታሮችን በማስፋት የአርሶ አደሩን ትርፍ አምራች በማድረግ የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባሻገር ኢኮኖሚያዊ አቅሙን የማሳደግ ስራ ታሳቢ ተደርጎ እየተከናወነ ነው። እንዲሁም እንደ ሀገር በምግብ እህል ራስን የመቻል ግብ እንዲሳካ በሚያግዝ አግባብ እየተከናወነ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ለመስኖ ተቋማት ግንባታና ተያያዥ ስራዎች ከ1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ ወጭ መደረጉንም ምክትል ቢሮ ኃላፊው አስታውቀዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም ቀደም ሲል ግንባታቸው ተጀምሮ ያልተጠናቀቁ እና አዳዲስ ፕሮጀክቶችን ወደ ግንባታ በማስገባት ዕቅድ ተይዞ ወደ ስራ እየተገባ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ በመስኖ መልማት የሚችል ከ 2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት እንዳለም ከቢሮው የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
በባሌ ዞን በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎች በተሞክሮነት የሚወሰዱ ናቸው
Jul 29, 2026 1992
ሮቤ፣ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ)፦በባሌ ዞን በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎች በተሞክሮነት የሚወሰዱ መሆናቸውን የብልጽግና ፓርቲ የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን የመስክ ምልከታ እያካሄዱ ነው።   አመራሮቹ ''ውጤታማ ተግባቦት ለጠንካራ ፓርቲ''በሚል መሪ ሐሳብ ለሁለት ቀናት በባሌ ሮቤ ሲያካሂዱት የነበረውን የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ግምገማ መድረክ ካጠናቀቁ በኋላ ነው የመስክ ምልከታውን የጀመሩት። በብልፅግና ፓርቲ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት፤ በዞኑ የአርሶ አደሩን ሕይወት ለማሻሻል በግብርናው መስክ እየተከናወኑ የሚገኙ ሥራዎች በተሞክሮነት የሚወሰዱ ናቸው። በተለይ አርሶ አደሩ የተሻሻሉ የግብርና አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ በኩታ ገጠም ልማት እያከናወነ የሚገኘውን ጥረት በማሳያነት አቅርበዋል። እንዲሁም ዞኑ ዝናብና የሌሎች የውኃ አማራጮችን በመጠቀም በዓመት ሁለት ጊዜና ከዚያ በላይ ማልማት የሚቻልበት መሆኑን በመስክ ምልከታው ማረጋገጣቸውን ገልጸዋል። በየደረጃው የሚገኙ አርሶ አደሮች ከሚያለሙት ልማት ተጠቃሚ በመሆን፣ ኮምባይነርና ትራክተር በመግዛት ወደ ግብርና ሜካናይዜሽን እየተሸጋገሩ መምጣታቸውንም ተናግረዋል። ይህም በሀገር አቀፍ ደረጃ የግብርናውን ዘርፍ ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የገጠር ሽግግርን ለማፋጠን ያለው እገዛ ከፍተኛ መሆኑንም አክለዋል።   የብልፅግና ፓርቲ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች የመስክ ምልከታ የዞኑን ነባራዊ ሁኔታ በመረዳትና በማስተዋወቅ፣ ወደየአካባቢያቸው ሲመለሱ የቀሰሙትን ልምድ እንዲያሰፉ ዕድልን ይፈጥራል ብለዋል። በዞኑ በዘንድሮ የበልግ ወቅት ከ240 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል ዘሮች የተሸፈነ ሲሆን፣ ከልማቱም ከ8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ የገለጹት ደግሞ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሀኪም አልይ ናቸው። በተለያዩ የሰብል ዘሮች እየለማ ከሚገኘው ልማት 80 በመቶ የሚሆነው በሜካናይዜሽን በመታገዝ በኩታ ገጠም አሰራር የለማ መሆኑንም ተናግረዋል።   በዞኑ በመኸር፣ በበልግና በመስኖ አማራጮች ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚለማ ሲሆን፣ ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ዓመታዊ ምርት እንደሚመረትም አመልክተዋል። ለዚህም በልዑካን ቡድኑ የተጎበኘው የበጋ ስንዴ ልማት አንዱ ማሳያ መሆኑን ያነሱት ዋና አስተዳዳሪው፤ ጉብኝቱ በዞኑ የሚገኙ አማራጮች ይበልጥ እንዲተዋወቁ ዕድል መፍጠሩንም ገልጸዋል። የአመራር አባላቱ በሮቤ ከተማ መደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ ''ተስፋን እንትከል'' በሚል መሪ ሀሳብ ዐሻራቸውን ያኖሩ ሲሆን፣ ጉብኝታቸውን በመቀጠልም የአካባቢውን የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎች እንደሚጎበኙም ታውቋል።
በክልሉ በሰላም፣ በልማትና መልካም አስተዳደር የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ስራዎች ተከናውነዋል-ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰዉ (ዶ/ር)
Jul 29, 2026 1229
ሆሳዕና ፤ ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት አመት በሰላም፣ በልማትና መልካም አስተዳደር የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ስራዎች መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። "ሁሉ አቀፍ እመርታ ፣ ለሁለንተናዊ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ በክልሉ የ2018 በጀት ዓመት የፓርቲና የመንግስት ስራዎች አፈፃፀምና የ2019 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ የከፍተኛ አመራሮች የዉይይት መድረክ በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ነው።   ርዕስ መስተዳድሩ በወቅቱ ባደረጉት ንግግር በክልሉ በ2018 በጀት ዓመት በፓርቲና በመንግሥት ስራዎች አፈፃፀም ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል። በሰላም፣ በልማትና መልካም አስተዳደር የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ስራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል። የህዝቦችን አብሮነት በማጠናከር ክልሉን የህብረ ብሄራዊነት ተምሳሌት ለማድረግ በተሰሩ ስራዎች ውጤት መመዝገቡን አመልክተዋል። በበጀት ዓመቱ የተገኙ ስኬቶችን ማጠናከርና የተስተዋሉ ጉድለቶችን በማረም ቀጣይ አቅጣጫ ማስቀመጥ የመድረኩ ዋና ዓላማ ስለመሆኑም ገልጸዋል። በመድረኩ የክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ፋጤ ሰርሞሎ ፣ በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ዕህፈት ቤት ሀላፊ ዲላሞ ኦቶሬ (ዶ/ር) ጨምሮ የክልል ፣ የዞን ፣ የልዩ ወረዳ ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች እየተሳተፉ ነው።  
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 9 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ አገኘ
Jul 29, 2026 1804
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ) :-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 9 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን የግሩፑ ዋና ስራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ። አየር መንገዱ በ2018 በጀት ዓመት ውጤማ የስራ እንቅስቃሴ ማድረጉንም ዋና ስራ አስፈጻሚው ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው በሰጡት መግለጫ እንዳሉት፤ አየር መንገዱ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 9 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል። ገቢው ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ20 በመቶ ብልጫ እንዳለው ጠቅሰው፤ በ2018 በጀት ዓመት ከተያዘው ዕቅድ ጋር ሲነጻጸር የ9 በመቶ ብልጫ አለው ብለዋል። አራት አዳዲስ ዓለም አቀፍ የበረራ መዳረሻዎች መክፈቱን ጠቁመው፤ 20 ነጥብ 7 ሚሊዮን መንገደኞችን ማጓጓዙን ተናግረዋል።   22 የነበሩ የሀገር ውስጥ መዳረሻዎች ወደ 25 ከፍ እንዲል መደረጉን ጠቁመው፤ ይህም የሀገር ውስጥ አገልግሎት አቅም ከፍ ያደረገ ነው ብለዋል። 897 ሺህ ቶን ጭነት የማጓጓዝ አገልግሎት መስጠቱን ገልጸው፥ ይህም ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ16 በመቶ ብልጫ እንዳለው አስረድተዋል። እንደ አቶ መስፍን ገለጻ አየር መንገዱ በበጀት ዓመቱ 9 አዳዲስ አውሮፕላኖች በግዥ እና በኪራይ ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉ የተሻለ ውጤት እንዲመጣ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ጠቅሰዋል።
በሸገር ከተማ ባለፈው በጀት ዓመት ከቱሪዝም ዘርፍ ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተገኝቷል
Jul 29, 2026 1132
ሸገር፣ ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ)፡-በሸገር ከተማ በ2018 በጀት ዓመት ከቱሪዝም ዘርፍ ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን የከተማው አስተዳደር አስታወቀ። የሸገር ከተማ አስተዳደር ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ቢንያም ፀጋዬ በ2018 በጀት ዓመት በከተማው ያለውን የተፈጥሮ እና ሰው-ሰራሽ የቱሪዝም መስህቦችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በከተማው የቱሪዝም መሠረተ ልማትን በማስፋፋት ወደ ከተማዋ የሚደረገውን የቱሪስቶች ፍሰት ለመጨመር የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቁመዋል። በከተማዋ ጥንታዊና ታሪካዊ የሃይማኖት ተቋማትን፣ በገፈርሳ ሐይቅ የሚካሄዱ የእሬቻና መልካ አቴቴን የመሰሉ የኦሮሞ ህዝብ በዓላት የሚከበሩባቸውን ስፍራዎች በማልማት የቱሪስቶች ፍሰት እንዲጨምር ጥረት መደረጉን ተናግረዋል። በተጨማሪም የተለያዩ እንስሳትና አእዋፋት የሚገኙበት የኤግዱ እላላ፣ ሌሎች ውብ ተራሮችና አስደናቂ የመሬት አቀማመጦችን ለቱሪስት ምቹ በማድረግ፣ የቱሪስቶችን ፍሰት ከማሳደግም ባለፈ የቆይታ ጊዜያቸውን እንዲያራዝሙ መደረጉን ገልጸዋል። በዚህም በ2018 በጀት ዓመት 500 ሺህ የሀገር ውስጥ ጎብኚዎችን ለማስተናገድ በማቀድ በተደረገው እንቅስቃሴ ከ1 ሚሊዮን በላይ በሚሆኑ ጎብኚዎች ከዕቅድ በላይ መፈፀም መቻሉን ተናግረዋል። እንዲሁም ከ25 ሺህ በላይ የሚሆኑ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች ከተማዋን መጎብኘታቸውን ኃላፊው ጠቁመው፣ በአጠቃላይ ከቱሪዝም ዘርፉ ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ተናግረዋል። በከተማዋ በተከናወኑ ተግባራት ዘርፉ ገቢን ከማስገኘት ባለፈ ለዜጎች በርካታ የሥራ እድሎችን እየፈጠረ መሆኑንም አብራርተዋል። በ2019 በጀት ዓመትም በከተማዋ የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎችን በማልማትና በማስፋፋት፣ የከተማዋን የቱሪስት ፍሰት ለመጨመርና የቆይታ ጊዜ ለማራዘም የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ መሆናቸውንም አስረድተዋል።  
በደቡብ ጎንደር ዞን በሩዝ ሰብል ለማልማት ከታቀደው ውስጥ 91 በመቶውን ለማሳካት ተችሏል- መምሪያው
Jul 29, 2026 1111
ጎንደር፤ ሐምሌ 22 /2018 (ኢዜአ) ፡-በደቡብ ጎንደር ዞን በያዝነው ክረምት በሩዝ ሰብል ለማልማት ከታቀደው 107 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ 91 በመቶውን በዘር መሸፈን መቻሉን የዞኑ ግብርና መመሪያ አስታወቀ። ​የመመሪያው ኃላፊ አቶ የሺጥላ አፍቃዴ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የሩዝ ልማት ስራው አርሶ አደሩ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ ከማድረግ ባሻገር ለገበያ የሚቀርብ ምርት እንዲኖረው አድርጓል።   ​በተያዘው ክረምትም በፎገራ ፣ ሊቦከምከምና ደራ ወረዳዎች 107 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ ሰብል ለመሸፈን ታቅዶ እስከ አሁን በተደረገው ጥረት 91 በመቶውን ለማሳካት ተችሏል ነው ያሉት። ​አርሶ አደሩ ቴክኖሎጂንና ግብአትን በአግባቡ በመጠቀም በሩዝ ልማት ስራው ምርታማነቱን እንዲያሳድግም የባለሙያዎች ድጋፍና ክትትል እየተደረገለት መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ባለፈው ዓመት የመኸር ወቅት በሄክታር በአማካይ የተገኝውን 56 ኩንታል የሩዝ ምርት በዘንድሮው ዓመትም ወደ 65 ኩንታል ለማሳደግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ያስችላል ብለዋል። ​አሁን ላይ የሩዝ ልማት ከመስፋፋቱና ምርታማነቱ ከማደጉ ጋር ተያይዞ አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለሀገር ውስጥ ገበያ የማቅረብ አቅም መገንባቱን አስረድተዋል። ከአካባቢው የአየር ንብረት ሁኔታ ጋር የተቀናጀው የሩዝ አመራረት ሂደት፣ የምግብ ዋስትና በአስተማማኝ ሁኔታ ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ከማገዝ ባለፈ አርሶ አደሩ ለገበያ የሚተርፍ ምርት እንዲያገኝ አድርጓል ብለዋል። በወረታ ከተማ አስተዳደር የወረታ ዙሪያ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር አብራራው ጀግኔ፤ በሩዝ ልማት ስራ ምርታማነታቸውን በማሳደግ ሃብት ለመፍጠር እንደቻሉ ነው የሚናገሩት። በዘንድሮው ዓመትም በአንድ ሔክታር መሬት ላይ የተሻሻሉ የሩዝ ዘርና ግብአት ተጠቅመው በመዝራት የተሻለ ምርት ለማግኝት እየሰሩ መሆኑን አመልክተዋል። ሌላው የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ዳኛው አልጣህ በበኩላቸው፤የነበራቸው መሬት ውኃ የሚተኛበት በመሆኑ ከሚዘሩት ጤፍና ኑግ በቂ የሆነ ምርት ስለማይገኝ ለተረጂነት ተጋልጠው እንደቆዩ ነው የሚናገሩት። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ተግባራዊ የተደረገው የሩዝ ልማት ስራ ውሃማ አካባቢን የሚፈልግ በመሆኑ ምርታማ በመሆን ሃብት ለመፍጠር መቻላቸውን ነው የገለጹት። ገለባውንና ተረፈ ምርቱንም በመኖነት በመጠቀም ከብት በማደለብ እና በወተት ልማት በመሰማራት በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የሚገልጹት።  
የኢንዱስትሪ ምርቶች ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትና ለውጭ ገበያ የማቅረብ አቅም እያደገ መጥቷል-ሚኒስትር መላኩ አለበል
Jul 29, 2026 1158
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርቶች ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የማሳደግና እና ለውጭ ገበያ የማቅረብ አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ። ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማ እና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ መድረክ አካሂዷል።   በተጨማሪም ሚኒስቴሩ በበጀት ዓመቱ ወደ ውጭ የመላክ የላቀ አፈጻጸም ላሳዩ አምራች ኢንዱስትሪዎች የእውቅና እና የምስጋና መርሃ ግብር አካሂዷል። ሚኒስትር መላኩ አለበል በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ በሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ የላቀ ሚና አበርክቷል። በአምራች ዘርፉ የሚመሩ የተለያዩ ስትራቴጂዎችን በመቅረጽ ዘርፉን የማነቃቃትና የመደገፍ ሥራ መሠራቱንም ጠቁመዋል። የኢንዱስትሪ ካውንስል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አማካኝነት ተቋቁሞ፣ የኢንዱስትሪዎችን ችግር ከመለየት ጀምሮ በዘላቂነት ተወዳዳሪ ሊሆኑ የሚችሉበትን አሰራር መዘርጋቱን ገልጸዋል። በዚህም በዘርፉ የነበሩ ማነቆዎች ለይቶ መፍትሔ በመስጠት ምርት እና ምርታማነት በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪ ችግሮች እንዲፈታ ታስቦ ተግባራዊ መሆን ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በዘርፉ ከፍተኛ ውጤቶች መመዝገባቸውን አመላክተዋል።   ይህ ንቅናቄ ሥራ አቁመው የነበሩ በርካታ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ እንዲመለሱ ማድረጉን እና አዳዲስ ኢንቨስትመንቶችም እንዲሰማሩ ማስቻሉን ተናግረዋል። በዚህም ገቢ ምርቶችን በመተካት እና የወጭ ንግድን በማሳደግ ረገድ የማይተካ ሚና ማበርከቱን ጠቁመዋል። የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የፋይናንስ ማነቆ ለመፍታት በተወሰደ እርምጃ፣ ቀደም ሲል 40 ቢሊዮን ብር የነበረውን የብድር መጠን ወደ 115 ቢሊዮን ብር ከፍ ማድረግ ተችሏል። "ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ በተጀመረበት ወቅት ለአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ ይቀርብ የነበረው የውጭ ምንዛሬ መጠን አሁን ላይ ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ማድረስ መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም የኢንዱስትሪዎቻችን ተወዳዳሪነት፣ ምርታማነት፣ ትርፋማነት እና የመስፋፋት ዕድል ከፍ እያለ መምጣቱን ገልጸዋል። ከ2014 በፊት ኢንዱስትሪዎች ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በመተካት ረገድ ከ348 ሚሊዮን ዶላር በላይ የሚያድኑ አልነበሩም ያሉት ሚኒስትሩ፣ አሁን ላይ ግን 5 ነጥብ 9 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን ተናግረዋል።   ይህም የንግድ ሚዛንን በማጣጣሙ በኩል የኢትዮጵያን ዘላቂ ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ ከፍተኛ ድርሻ ማበርከቱን አብራርተዋል። በወጭ ንግድ በኩል ቀደም ሲል ይገኝ የነበረው 385 ሚሊዮን ዶላር በዚህ ዓመት ወደ 607 ሚሊዮን ዶላር ማደጉን ጠቁመው፤ የአምራች ዘርፉ ለሥራ ዕድል ፈጠራም ትልቅ አማራጭ እየሆነ መምጣቱን ጠቁመዋል። በ2019 በጀት ዓመት ከወጭ ንግድ የሚገኘውን ገቢ ወደ 1 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን ገልጸው፣ ይህንን ዕቅድ ለማሳካት ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እንደሚሠራም አረጋግጠዋል። በእውቅናና ምስጋና መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት አምራቾች በበኩላቸው፤ በኢንዱስትሪው ዘርፍ የተደረጉ የፖሊሲ ማሻሻያዎችና አዳዲስ አቅጣጫዎች ለዘርፉ አዎንታዊ ሚና ማበርከታቸውን ገልጸዋል፡፡   ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል አቶ ሀብታሙ ዳርጌ፤ የተደረጉት የፖሊሲ ማሻሻያዎች የሪፎርም ስራዎች ለአምራቾች ትልቅ ዕድል ይዞ መምጣቱን ጠቅሰዋል፡፡   ማሻሻያዎቹ የምርት መጠናቸውንና ምርታማነታቸውን በከፍተኛ ደረጃ እንዳሳደገላቸው የገለጹት ደግሞ ህይወት ዳመኑ ናቸው።
በምስራቅ ሸዋ ዞን በመኸር ወቅት እርሻ ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል
Jul 29, 2026 1080
አዳማ፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ)፦በምስራቅ ሸዋ ዞን በመኸር ወቅት እርሻው ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት መታቀዱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለፀ። የምስራቅ ሸዋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ታቅዶ እየተሰራ ነው።   በዞኑ በዘንድሮው የመኸር ወቅት ለማልማት ታቅዶ ከነበረው ከ530 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ውስጥ እስካሁን ከ475 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በተለያየ ምርጥ ዘር መሸፈኑን ተናግረዋል። ለዚህም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር መዳበሪያ ለማቅረብ መታቀዱን ጠቅሰው፣ እስካሁን ከ800 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ መቅረቡን ገልጸዋል። የታቀደውን ምርት ለማግኘትም የግብርና ቴክኖሎጂ፣ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ በስፋት ጥቅም ላይ መዋሉን ጠቅሰው፤ለአርሶ አደሩም ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ነው ብለዋል። የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የግብርና ምርቶችን የኤክስፖርት አቅም ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት ለመደገፍ በዕቅድ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የኤክስፖርት ምርቶችን ለመጨመር በስንዴ፣በቦሎቄና በሽንብራ ላይ በሜካናይዜሽን የተደገፈ የኩታ ገጠም የሰብል ልማት እየተከናወነ መሆኑንም አክለዋል። የዞኑን ግብርና ከበሬ ማረስ በማውጣት ወደ ሜካናይዜሽን ለማሸጋገር በተያዘው ዓመት 155 የእርሻ ትራክተሮች ተገዝተው በልማት ስራ ላይ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በዞኑ ስንዴ፣ ቦሎቄ፣ ሽንብራ፣ ጤፍና ሌሎች ዋና ዋና ሰብሎች በ460 ክላስተር በመደራጀት እየለሙ መሆናቸውን ምክትል ኃላፊው አስረድተዋል።
በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ93 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰብስቧል
Jul 28, 2026 425
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 21/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ93 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ እንደተቻለ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ። የባህር ዳር ከተማ ገቢዎች መምሪያ "ግብሬን ደስ ብሎኝ እከፍላለሁ" በሚል መሪ ቃል የ2018 አፈፃፀም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት እቅድ ትውውቅ መድረክ አካሂዷል።   የቢሮ ኃላፊው መንገሻ ፈንታው(ዶ/ር) እንደገለጹት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ93 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ ስኬታማ ስራዎችን አከናውኗል ። ቢሮው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ100 ነጥብ ሶስት ቢሊዮን በላይ ለመሰብሰብ አቅዶ ሲሰራ የቆየ ሲሆን የእቅዱን 92 በመቶ ማሳካት መቻሉን ገልጸዋል። የተሰበሰበው ገቢ ለክልሉ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እድገት በማዋል በራስ የመልማት አቅም ለመገንባት የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ነው የተናገሩት። ቢሮው ከባህዳር ዩኒቨርሲቲና ከኢትዮ-ቴሌኮም ኩባንያ ጋር በመተባበር በዲጂታል ግብር የመክፈል ስርአት መዘርጋቱ ለዘርፉ ውጤታማነት አስተዋጽኦ ማበረከቱን አስረድተዋል። ይህም ደንበኞች ባሉበት ቦታ ሆነው ግብር በመክፈል ፈጣን፣ ተአማኒነት ያለውና ፍትሃዊ አገልግሎት እንዲያገኙ በማድረግ የመልካም አስተዳደር ችግርን ለመቅረፍ የሚያስችል መሆኑን አስገንዝበዋል።   የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ኃይለማርያም እሸቴ በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ዘጠኝ ቢሊዮን ብር ገቢ በመሰብሰብ የዕቅዱን 91 በመቶ ማሳካት ተችሏል ብለዋል። በተሰበሰበው ገቢም በከተማዋ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች የልማት ስራዎችን በማከናወን የህዝቡን የመልማት ጥያቄ ለመመለስ የሚውል እንደሆነም አስረድተዋል። በ2019 በጀት ዓመትም የግብር አሰባሰብ ስርአቱን ይበልጥ ግልጽ፣ ፍትሐዊና በህዝብ ዘንድ ተአማኒነት ያለው ለማድረግ በተሻለ መንገድ እንደሚሰራ አስገንዝበዋል። በመድረኩ ማጠናቀቂያ ላይም ለምስጉን ግብር ከፋዮችና ከፍተኛ ገቢ ለሰበሰቡ ተቋማት እውቅና የመስጠት ስነ ስርአት ተካሂዷል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም