ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ኢትዮጵያ ከዩናይትድ ኪንግደም ጋር የዓለም ንግድ ድርጅት የሁለትዮሽ ገበያ ዕድል ስምምነት ተፈራረመች
Aug 20, 2026 85
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦​ኢትዮጵያ ከዩናይትድ ኪንግደም ጋር በዓለም ንግድ ድርጅት (WTO) አባልነት ሂደት ማዕቀፍ ስታካሂድ የቆየችውን የሁለትዮሽ የገበያ ዕድል ድርድር በስኬት በማጠናቀቅ የስምምነት ሰነድ ተፈራርማለች። ​የስምምነት ሰነዱን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት ዋና ተደራዳሪ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር እና በኢትዮጵያ የዩናይትድ ኪንግደም አምባሳደር ዳረን ዌልች ተፈራርመውታል። ​በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ይህ ታሪካዊ ስምምነት የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም እና የፖሊሲ ምህዳር ሙሉ በሙሉ ባስጠበቀ መልኩ የተከናወነ ነው ብለዋል። አክለውም ስምምነቱ የሁለቱን ሀገራት የቆየ ዲፕሎማሲያዊ፣ የንግድ እና የኢንቨስትመንት ትስስር ይበልጥ የሚያጠናክር ከመሆኑም በላይ፣ ኢትዮጵያ በዓለም ንግድ ድርጅት ሙሉ አባል ለመሆን የምታደርገውን ጥረት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ወሳኝ ስኬት መሆኑን አብራርተዋል። የዩናይትድ ኪንግደም አምባሳደር ዳረን ዌልች በበኩላቸው፤ የተደረገው ስምምነት የሁለቱን ሀገራት የቆየ የኢኮኖሚና የዲፕሎማሲ ግንኙነት ይበልጥ የሚያጎለብት መሆኑን ገልጸዋል። ዩናይትድ ኪንግደም ኢትዮጵያ ወደ ዓለም ንግድ ድርጅት ለመቀላቀል የምታደርገውን ጥረት እና የምታካሂዳቸውን የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች በሙሉ ቁርጠኝነት መደገፏን የምትቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። ​ኢትዮጵያ እስካሁን ባለው ሂደት ከቻይና፣ ሩሲያ፣ አርጀንቲና፣ ቱርክ፣ ብራዚል፣ ጃፓን፣ ሕንድ፣ ኒውዚላንድ እና ታይላንድ ጋር ተመሳሳይ ስምምነቶችን ተፈራርማለች። ዩናይትድ ኪንግደም ስምምነቱን በይፋ ከፈረሙ አባል ሀገራት 10ኛዋ እና ድርድሩን በስኬት ካጠናቀቁት ደግሞ 11ኛዋ አባል ሀገር ሆናለች።
ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝ ሀብቷን ለማልማት ከማንም ፈቃድ አያስፈልጋትም - የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር)
Aug 20, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝ ሀብቷን የመጠቀም እና የማልማት ሉዓላዊ መብት ስላላት ከማንም አካል ፈቃድ መጠየቅ እንደማያስፈልጋት የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስትሩ አክለውም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ኤሌክትሪክ ኃይል በማመንጨት ለቀጣናው የሚተርፍ ሀብት መሆኑንም አመልክተዋል። ሚኒስትሩ ከፐልስ ኦፍ አፍሪካ (The Pulse of Africa) ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የተገነባው ለኃይል ማመንጨት ብቻ እንደሆነና አዎንታዊ ሚናውን ቀጣናዊ የኤሌክትሪክ ግብይትን በማስፋት ከኢትዮጵያ ድንበር የተሻገረ ጠቀሜታ እንዳለውም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለጎረቤት ሀገራት ማለትም ለጅቡቲ፣ ለኬንያ እና ለሱዳን የኤሌክትሪክ ኃይል በማቅረብ ላይ እንደምትገኝ የጠቆሙት ሚኒስትሩ፣ ከሶማሊያ እና ከደቡብ ሱዳን በኩል ያለው የኢነርጂ ፍላጎት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱንም አብራርተዋል። የዓባይ ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት (CFA) እና የዓባይ ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ የወንዙን የጋራ ጥቅም ለማሳደግ የተደረጉ ጥረቶች ማሳያ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በሌሎች ድንበር ተሻጋሪ የዓለም ወንዞች ላይ ባለው ተሞክሮ ትብብርን የሚጀምሩት የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ቢሆኑም፣ በዓባይ ጉዳይ ግን እንተባበር በማለት ውይይቱን በግንባር ቀደምትነት ስትመራ የቆየችው ኢትዮጵያ መሆኗን አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ከሕዳሴ ግድብ በታች የሚገኙ ሊለሙ የሚችሉ መሬቶቿን ከመስኖ ልማት ውጪ ማድረጓ ለታችኞቹ የተፋሰሱ ሀገራት ያላትን ትልቅ ግምት እንደሚያሳይ ሚኒስትሩ አክለው ገልጸዋል። በቴክኒክ ደረጃ፣ ከግድቡ በታች ከ230 ሺህ ሄክታር በላይ የመስኖ ልማት የሚሆን መሬት አለን፤ ነገር ግን በታችኛው ተፋሰስ በኩል ያለውን ፍላጎት ስለምናውቅ ይህንን አላደረግነውም ሲሉ አስረድተዋል። ሚኒስትሩ የህዳሴ ግድብ ኃይል ካመነጨ በኋላ የሚለቀቀው ውሃ ቀጥታ ወደ ታችኛው ተፋሰስ ወደሚገኙ ወንድም ሀገራት እንደሚፈስ በመግለጽ ኢትዮጵያ ለጋራ ተጠቃሚነት ያላትን ቁርጠኝነት አንስተዋል። ሚኒስትሩ ሕዳሴ ግድብን በጋራ ለማስተዳደር የሚቀርቡ ጥሪዎችን ውድቅ ያደረጉ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ሌሎች ሀገራት በግድቡ ላይ ቁጥጥር የሚደረጉበትን አሰራርን አትቀበልም ብለዋል። በኢትዮጵያውያን ገንዘብ የተገነባውን፣ ኩራታችን እና ብሔራዊ የክብር ፕሮጀክታችን የሆነውን ግድብ፣ ግንባታውን ሲቃወም የነበረ አካል መጥቶ በጋራ እናስተዳድር እንዴት ሊል ይችላል? ሲሉ ጠይቀዋል። ይህ ፈጽሞ የማይቻል፣ በፍፁም ሊታሰብ የማይችል ነው ሲሉም ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የዓባይ ተፋሰስ ሀገራት የኢትዮጵያን የልማት መብት ለመገደብ ከመጣር ይልቅ በውይይት እና በትብብር ላይ ትኩረት ማድረግ አለባቸው የሚል የጸና አቋም እንዳላት ተናግረዋል።
በመዲናዋ የተገነቡ የመዝናኛ ፓርኮች አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን ከዘመናዊ የቱሪዝም መስህቦች ጋር አስተሳስራ እንድትቀጥል አስችለዋታል
Aug 20, 2026 171
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦በመደመር መንግሥት በመዲናዋ የተገነቡት የመዝናኛ ፓርኮች አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን ከዘመናዊ የቱሪዝም መስህቦች ጋር አስተሳስራ እንድትቀጥል ማስቻላቸውን የአንድነት ፓርኮች ኮርፖሬሽን ገለጸ። በመዲናዋ የተገነቡት ፓርኮች ልዩ ልዩ ሁነቶችን ማከናወን የሚያስችሉ መሰረተ ልማቶች የተሟላላቸው እና ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠር ማስቻላቸውም ተመላክቷል። የመደመር መንግሥት ቱሪዝምን አንዱ የኢኮኖሚ ምሰሶ በማድረግ በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገር እና ገበታ ለትውልድ ተነሳሽነቶች አማካኝነት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ዘመናዊ የቱሪስት መዳረሻዎችን ገንብቷል። እነዚህ ግዙፍ የቱሪዝም መዳረሻ የልማት ሥራዎች የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎችን ቀልብ በመሳብ ኢትዮጵያን ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ በማድረግ ከዘርፉ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ አስችለዋታል። በገበታ ለሸገር ከተገነቡት የቱሪዝም መዳረሻዎች መካከል የአንድነት ፓርክ የመዲናዋን ማራኪነት በማጎልበት በጎብኚዎች ተመራጭ እንድትሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ወዳጅነት ፓርክ አንድ እና ሁለት አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ገጽታዋን ከዘመናዊ ቱሪዝም ጋር አጣጥማ እንድታስቀጥል ምቹ ዕድል ፈጥረዋል። የአንድነት ፓርኮች ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ነጃት ግርማ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ ፓርኮቹ ባለፉት ዓመታት በርካታ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ጎብኚዎችን መሳብ ችለዋል። የፓርኮቹ ተገንብቶ አገልግሎት መስጠት ለበርካታ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም ተናግረዋል። በተጨማሪም ፓርኮቹ የተለያዩ ሁነቶችን በማስተናገድ ከፍተኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እንዲፈጠር ማስቻላቸውን ጠቁመዋል፡፡ ይዘት ፈጣሪዎች ሥራዎቻቸውን የሚያከናውኑበት ተመራጭ ማዕከል መሆን መቻላቸውን ጠቅሰው፤ የተለያዩ የንግድ ተቋማት በፓርኩ ሥራቸውን በተሻለና ምቹ በሆነ መልኩ እንዲያከናወኑ ማድረጉን ተናግረዋል። ይህም የኢኮኖሚ ፍሰቱን በማሳለጥ በኩል አወንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በፓርኩ ሲዝናኑ ያገኘናቸው ወጣቶች በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በቱሪዝም ዘርፍ ያላትን እምቅ አቅም ለመጠቀም እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የሚደነቁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡   ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል ናሆም ተስፋዬ፣ በአሁኑ ወቅት የአንድነት ፓርክን ጨምሮ በተለያዩ አካባቢዎች በርካታ የቱሪዝም መሠረተ ልማቶች መገንባታቸው በርካታ ጠቀሜታ እንዳላቸው ተናግሯል፡፡ ይህም ለሀገር ውስጥና ለውጭ ጎብኚዎች መሳብ እንዲሁም የኢትዮጵያን ገጽታ በመገንባት በኩል አበርክቷቸው ከፍተኛ መሆኑን ጠቁሟል፡፡ በመዲናዋ የተገነቡ እና እየተገነቡ የሚገኙ የቱሪስት መስህብ ስፍራዎች ለከተማዋ የቱሪዝም ዘርፍ መነቃቃት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን የገለጸችው ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ቤዛ ክፍሌ ናት፡፡   በከተማዋ የተገነባው የአንድነት ፓርክም ለጎብኚዎች ምቹ እና ተመራጭ የመዝናኛ ስፍራ ከመሆን ባለፈ ለቱሪዝም እድገት የራሱን ከፍተኛ ሚና እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጻለች፡፡   ሌላው አስተያየት ሰጪ ወጣት ሀንደሰ ዓለሙ በበኩሉ፣ አንድነት ፓርክ ለወጣቶች የስራ ትስስር እና የሀሳብና ልምዶችን የሚጋሩበት ምቹ አውድ መፍጠሩን ገልጿል፡፡  
አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን እያደገ መጥቷል- አርሶ አደሮች
Aug 20, 2026 127
መተማ፣ ነሐሴ14/2018 (ኢዜአ):- አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን የምዕራብ ጎንደር ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የቆላ ፍራፍሬ ልማትን በኩታ ገጠም አሠራር በሰፊው በማልማት አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታውቋል። አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን እያደገ መጥቷል። በዞኑ የመተማ ወረዳ አርሶ አደር ደሴ ባይተኩስ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መምጣት በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል። ባለፉት ዓመታት ካለሙት ሙዝና ማንጎ ልማት ብቻ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ150 ሺህ ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘታቸውንም ገልጸዋል። "በተለይም በክላስተር በመደራጀታችን የውኃ አጠቃቀማችንና የግብዓት አቅርቦታችንን ለማስተካከል አስችሎናል" ያሉት አርሶ አደሩ፣ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በስፋት የፍራፍሬ ችግኞችን መትከላቸውን ተናግረዋል።   በወረዳው የመንደር 6 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ፀጋነሽ ብዙነህ በበኩላቸው፣ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት በመሳተፋቸው ተጨማሪ ገቢ ማግኘት እንደቻሉ ገልጸዋል። እስካሁን ሁለት ሄክታር የሚጠጋ መሬትን በሙዝ፣ በማንጎና በፓፓያ ማልማታቸውን ጠቁመው፣ ምርቱን ለቤት ውስጥ ፍጆታ ከማዋል ባሻገር የተረፈውን በመሸጥ በዓመት ከ100 ሺህ ብር በላይ ገቢ እንደሚያገኙ አስረድተዋል። አርሶ አደር ፀጋነሽ አክለውም፣ የአረንጓዴ ልማቱ የመሬቱን ለምነት በመጨመር ከሰብል ልማት በተጨማሪ በፍራፍሬ ልማትም ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረጉን ጠቁመው፣ ያገኙትን ውጤት ለማስቀጠል እንደሚተጉም ገልጸዋል።   የምዕራብ ጎንደር ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ እንደገለጹት፣ በዞኑ በ1 ሺህ 113 ሄክታር መሬት ላይ ቡናና የቆላ ፍራፍሬ የማልማት ሥራ እየተካሄደ ይገኛል። እስካሁን 117 አልሚ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማቱ በኩታ ገጠም እየተካሄደ እንደሚገኝ ጠቁመው፣ በዚሁ አሠራር ከ40 ሄክታር በላይ መሬት በፓፓያና በሙዝ ለምቷል ብለዋል። የምዕራብ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ በአሁኑ ወቅት እየታየ ያለውን አዎንታዊ ውጤት ከአረንጓዴ አሻራ ልማቱ ጋር ይበልጥ በማስተሳሰር የማስፋፋት ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጧል።  
የእንሰት ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረጉ የምርምር ሥራዎች ይጠናከራሉ
Aug 20, 2026 108
​ወልቂጤ፣ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡-የእንሰት ተክልን ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት አስታወቀ፡፡ እንሰት ለብዙ ኢትዮጵያውያን የዕለት ተዕለት የምግብ ዋስትና መሠረት በመሆኑ በእንሰት ላይ የሚካሄዱ የምርምር ሥራዎች በሽታን በመቋቋም ምርታማነትን የማሳደግ እና ባህላዊ አሰራርን የማዘመን ጠቀሜታው አላቸው። በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የግብርና ምርምር ማስተባበሪያ ጽህፈትቤት ሃላፊ መኩሪያ ታደሰ (ዶ/ር) እንዳሉት የእንሰት ልማት ከአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ ጋር በማጣጣም እየተከናወነ ይገኛል። ልማቱ የህብረተሰቡን የምግብ ዋስትንና ለማረጋገጥ እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በሚያስችል መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጡ የተሻሻሉ የእንሰት ዝርያዎች ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። በእንሰት ልማት ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንና በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በግብርና ሚኒስቴር የሥራ ሥርና እንሰት ልማት ዴስክ ኃላፊ አቶ ጉቱ ሚጀና እንደገለጹት፣ የእንሰት ልማትን ከአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጋር በማጣጣም እየተከናወነ ይገኛል።   ​እንሰት ከፍተኛ የምግብ ምርት የሚሰጥ፣ ድርቅን የሚቋቋም እና የአፈር እርጥበትን የመጠበቅ ተፈጥሯዊ ባህሪ ስላለው ለአረንጓዴ ልማት ሥራው ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል። የእንሰት ተክልን ምርታማነት ለማሳደግ በምርምር የተደገፈ ሥራ እየተከናወነ መሆኑንም አመልከተዋል። የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተርና ተመራማሪ አቶ ቤተል ነክር ማዕከሉ በበኩላቸው፣ በሽታን ተቋቁመው የተሻለ ምርት የሚሰጡ አዳዲስ የእንሰት ዝርያዎችን በስፋት አባዝቶ ለአርሶ አደሩ እያሰራጨ መሆኑን ተናግረዋል።   እንሰት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ብቻ በመጠቀም እንደሚለማ ገልጸው፣ ከአካባቢው አርሶ አደሮችና ሌሎች የምርምር ተቋማት ጋር በመቀናጀት ውጤታማ ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። እንሰት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የአየር ንብረትን ለማስጠበቅና የአፈር እርጥበትን ለመጠበቅ ጠቀሜታ እንዳለው የገለጹት ደግሞ የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ ናቸው።   ከምግብ ፍጆታነት ባለፈ የአርሶ አደሩ የገቢ ምንጭ እንዲሆንና ከተረፈ ምርቱም የተሻለ ጥቅም ለማግኘት የተሰሩ ሥራዎች ውጤት እያመጡ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በጉራጌ ዞን የእዣ ወረዳ አርሶ አደር ጀማል ሁሴን እና ወይዘሮ ነፃነት አርጋ በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የእንሰት ችግኞች በማግኘታቸው የተዳከመውን የእንሰት ልማት ሥራቸውን ለማጠናከር መቻላቸውን ገልጸዋል። ከዚህ በፊት ለእንሰት ተክል ብዙም ትኩረት እንደማይሰጡ አስታውሰው፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተሻሻሉ የእንሰት ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማ መሆን መቻላቸውን ተናግረዋል፡፡ የእንሰት ምርታማነትንና ተደራሽነትን ለማሳደግ በሚከናወኑ ተግባራት ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውንም አመልክተዋል።  
የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነትን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በቅንጅት የተከናወነው ተግባር ውጤታማ ነው
Aug 20, 2026 98
ደሴ፤ ነሐሴ 14/2018(ኢዜአ)፡- በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነትን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በቅንጅት የተከናወነው ተግባር ውጤታማ መሆኑን በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የደሴ ሪጅን ገለጸ። የሪጅኑ ዳይሬክተር አቶ ሀብቱ አበበ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነትን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በቅንጅት የተሠራው ሥራ ውጤታማ ነው። በዚህም በደሴ፣ በደቡብ ወሎ፣ በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር፣ በኮምቦልቻና አካባቢዋ 29 ሺህ 191 አዳዲስ ደንበኞችን የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ የተከናወነው ተግባር ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ9 ሺህ ደንበኞች ብልጫ እንዳለው የጠቆሙት ዳይሬክተሩ፣ ይህም በቅንጅትና በትብብር በመሥራት የመጣ ውጤት መሆኑን አስረድተዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም ከ43 ሺህ በላይ አዳዲስ ደንበኞችን የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ኅብረተሰቡም በአካባቢው የሚገኙ የኤሌክትሪክ ምሰሶዎችን፣ መስመሮችን፣ ትራንስፎርመሮችንና ሌሎች የመሠረተ ልማት አውታሮችን በንቃት እንዲጠብቅም አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የደሴ ሪጅን ከ250 ሺህ በላይ ደንበኞች እንዳሉት ከሪጅኑ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የሙዝ ምርት በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነቱን ለማሳደግ የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት ወሳኝ ነው
Aug 20, 2026 188
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦ የሙዝ ምርትን በዓለም አቀፍ ገበያ ያለውን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የጥራት ማሻሻያና የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት ወሳኝ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ አበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ አምራች ላኪዎች ማህበር የሙዝ ወጪ ንግድ ላይ ያተኮረ ሀገር አቀፍ ጉባዔ እያካሄደ ይገኛል፡፡   የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የሙዝ ምርት መጠን ቢኖርም ለውጭ ንግድ የሚቀርበው ለጎረቤት ሀገራት ብቻ ነው። ኢትዮጵያ ያላትን ለግብርና የተመቹ አግሮ-ኢኮሎጂያዊ ሁኔታዎች ወደ ሀብትና ካፒታል በመቀየር ዓለም አቀፍ የገበያ መዳረሻዎችን ማስፋት ይገባል ብለዋል። የመንግሥትና የግሉ ዘርፍ ትብብር በሆርቲካልቸር ዘርፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ ማድረጉን በማንሳት፤ በአትክልትና ፍራፍሬ ያለውን ተቋማዊ ልምድ፣ የሎጂስቲክስ እውቀት እና ዓለም አቀፍ የገበያ ትስስር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ሚኒስቴር ዘርፉን ገበያ ተኮር፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገርና ዘላቂ ለማድረግ በርካታ የፖሊሲ እና የስትራቴጂ ማዕቀፎችን ቀርጿል ብለዋል። የኢትዮጵያን ሆርቲካልቸር ዘርፍ ለማሳደግ የ10 ዓመት ብሔራዊ የሆርቲካልቸር ስትራቴጂ በመቅረጽ ለዘርፉ እድገት በቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም የሙዝ ምርት ዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የጥራት ማሻሻያና የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። በአበባና በአትክልት ዘርፍ የተገነባው ተቋማዊ ልምድ፣ የሎጂስቲክስ እውቀት እና ዓለም አቀፍ የገበያ ትስስር ለሙዝ ኢንዱስትሪው ስኬት መጠቀም ይገባልም ብለዋል።   የኢትዮጵያ አበባ አትክልትና ፍራፍሬ አምራች ላኪዎች ማህበር ዋና ዳይሬክተር ቴዎድሮስ ዘውዴ፤ በሆርቲካልቸር ኢንዱስትሪ ዘርፍ ያለውን እምቅ አቅም ለመጠቀም ከግብርና ሚኒስቴር እና ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየሠሩ መሆኑን ገልጸዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ በብዛት ከሚመረቱ የፍራፍሬ ዝርያዎች አንዱ መሆኑን ገልጸው፤ በኢትዮጵያ ከምግብነት ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የገቢ ምንጭና ሥራ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ከ18 ሺህ 800 ካሬ ሜትር በላይ የከተማ መሬት ወደ መሬት ባንክ እንዲገባ ተደርጓል
Aug 20, 2026 101
አዳማ ፤ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከ18 ሺህ 800 ካሬ ሜትር በላይ የከተማ መሬት ወደ መሬት ባንክ እንዲገባ መደረጉን የክልሉ ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ። የክልሉ ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር አብደላ ኦገቴ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተለያዩ ሴክተሮች ሙስና እና ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከል የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራትን አንስተዋል። በክልሉ በመንግስት ተቋማት የሚስተዋሉ ብልሹ አሰራሮችን አስቀድሞ ለመከላከል የሚያስችሉ 26 የሙስና መከላከል የአሰራር ስርዓት ጥናቶች መካሄዳቸውን ዘርዝረዋል። የመስኖ ፕሮጀክት ግንባታና የውል አስተዳደር፣ የሕገ-ወጥ ንግድ ክትትል እና የገቢ አሰባሰብ ስርዓት፣ የግል ህክምና ተቋማት የፈቃድ አሰጣጥና ክትትል፣ የአርሶ አደሮች ህብረት ሥራ ማህበራትና ዩኒየኖች የግዥና ሽያጭ አሰራር ጥናቶች የሚገኙበት መሆኑን ጠቅሰዋል። በተለይም በመሬት ሃብት ላይ የሚደርሰውን ምዝብራ ለመከላከል ብዙ ጥረት መደረጉን አስታውሰው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 18 ሺህ 849 ካሬ ሜትር የከተማ መሬት ወደ መሬት ባንክ ተመላሽ ተደርጓል ብለዋል። በዚህም የከተማ መሬትን ከህገ-ወጥ ወረራ፣ ከደላሎች ድብቅ ሽያጭ እና ከአሰራር ብልሹነት በመታደግ ወደ "መሬት ባንክ" ማስገባት፤ መሬቱ ለታለመለት ልማት እንዲውል ማድረግ እየተቻለ ስለመሆኑ አንስተዋል። በተጨማሪም በየደረጃው ለሚገኙ 6 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎች ግንዛቤ ለማስጨበጥ ታቅዶ፤ ከ10 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑት ተደራሽ በማድረግ ከእቅድ በላይ ማሳካት ስለመቻሉ ተናግረዋል። የሙስና ወንጀል ህጎች፣ የግዥና ግንባታ አስተዳደር ውል ህጎች፣ የሀብት ማስመለስ አዋጅ፣ የሙያ እና የአመራርነት ሥነ-ምግባር እንዲሁም የመከላከል ስትራቴጂዎች ላይ በማተኮር ግንዛቤ ስለመሰጠቱም አስታውሰዋል። ከ135 ሺህ በላይ የህዝብ ተመራጮች፣ ተሿሚዎች እና የመንግስት ሰራተኞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ የሃብት ምዝገባ ስራ ስለመካሄዱም ገልጸው በተያዘው ዓመትም መሰል ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። በሀገሪቷ በወጣው የሀብት ማስታወቂያና ምዝገባ አዋጅ ቁጥር 668/2002 መሠረት ተሿሚዎችና የመንግስት ሰራተኞች ሀብታቸውን እንዲያስመዘግቡ የሚደነግግ መሆኑ ይታወቃል።  
የሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር ዘላቂ ተጠቃሚነታችንን ለማረጋገጥ አስችሎናል-አርሶ አደሮች
Aug 20, 2026 106
ደብረብርሃን፤ ነሀሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡-በሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር በመሳተፍ ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ መቻላቸውን አርሶ አደሮች ገለጹ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የቤተሰብንና የሀገርን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ፣ የስነ-ምግብ አቅርቦትን ለማሻሻል እና የዜጎችን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት ተግባራዊ የተደረገ ወሳኝ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው። መርሃ ግብሩ በዋናነት የእንስሳት እና የዶሮ እርባታን፣ የወተት ምርትን፣ የ ማር እና የዓሣ ሀብት ልማትን በማስፋፋት አነስተኛ የቤት ውስጥ ምርታማነትን ወደ ላቀ የገበያ መር ምርት ማሸጋገርን ዓላማ ያደርጋል። በደብረብርሃን ከተማ አስተዳደር የባቄሎ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሰለሞን ሽፈራው ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለወተት ልማት ዘርፉ ልዩ ትኩረት በመስጠቱ በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ ለመሆን አስችሎናል።   በተለይም ዝርያቸው የተሻሸሉ የወተት ላሞችን በማራባት ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እንደቻሉ ነው የሚናገሩት። በተለይ የእንስሳት መኖ አቅርቦትና የአመጋገብ ሥርዓቱ እየተሻሻለ በመምጣቱ ከአንድ ላም በቀን በአማካይ 20 ሊትር ወተት ማግኘት ማስቻሉን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት በቀን ከ50 ሊትር በላይ ወተት ለሕብረት ሥራ ማህበራቸው በማቅረብ የተሻለ ገቢ እያገኙ መሆኑን ነው የጠቆሙት። በዚህም መኖሪያ ቤታቸውን ከማዘመን ባለፈ ገንዘብ ለመቆጠብና ሀብት ለማፍራት እንደቻሉ ገልጸዋል።   በተመሳሳይ በከተማ አስተዳደሩ የወሻውሽኝ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ጌታሁን ገነነ በበኩላቸው፣ ቀደም ሲል ከነበሯቸው የሀገር ውስጥ ላሞች በቀን ከአራት ሊትር ያልበለጠ የወተት ምርት ያገኙ እንደነበር አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት ግን የላሞችን ዝርያ በማሻሻል፣ በቂ መኖ በማዘጋጀትና የአመጋገብ ሥርዓቱን በማዘመን ከአንድ ላም በቀን እስከ 20 ሊትር ወተት ለማግኝት መቻላቸውን አስረድተዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ የእንስሳትና እንስሳት ተዋጽኦ ግብይት ቡድን መሪ አቶ ዳዊት አሳምነው በበኩላቸው፣ በበጀት ዓመቱ 37 ሚሊዮን 100 ሺህ ሊትር ወተት ለ44 አቀነባባሪዎች ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል።   በተጨማሪም የ2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ግምት ያለው የወተትና የወተት ተዋጽኦ ምርት ግብይት በመፈጸም አምራቾችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አብራርተዋል። የተገኘውንም ውጤት በአዲሱ የበጀት ዓመት በማስፋት አርሶ አደሩን ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሠራ እንደሚገኝ አመልክተዋል።    
በወልዲያ ከተማ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ11 ሺህ በላይ ለሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል- መምሪያው
Aug 20, 2026 90
ወልዲያ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡- በወልዲያ ከተማ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ለ11 ሺህ 768 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን የከተማ አስተዳደሩ ሥራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ መላኩ አለሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የከተማዋን ሰላም ከማረጋገጥ ጎን ለጎን ለወጣቶች የሥራ ዕድል የመፍጠር ተግባር ልዩ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ ነው። በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ለ9 ሺህ 268 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ ከእቅድ በላይ ለ11 ሺህ 768 ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል። ይህም ከዕቅዱ ጋር ሲነጻጸር 127 በመቶ አፈፃፀም ማስመዝገብ እንደተቻለ ነው ያመለከቱት። ከዕቅድ በላይ ማሳካት የተቻለው የአካባቢው ሰላም እየተሻሻለ በመምጣቱና የፖለቲካ አመራሩ ለዘርፉ ልዩ ትኩረት በመስጠቱ መሆኑንም አስረድተዋል። የሥራ ዕድሉ የተፈጠረው በከተማ ግብርና፣ በአምራች ኢንዱስትሪ፣ በብረታ ብረት፣ በአገልግሎትና በሌሎች ዕድገት ተኮር ዘርፎች መሆኑንም አብራርተዋል። ለሥራ ዕድል ተጠቃሚ ወጣቶች የብድር፣ የመሥሪያና የመሸጫ ቦታ (ሼድ) እንዲሁም የገበያ ትስስር ድጋፍ መደረጉንም አብራርተዋል። የስራ እድሉ ተጠቃሚ የሆነች የወልድያ ከተማ ነዋሪ ወጣት እመቤት ደምሴ፤ በተደረገላት ድጋፍ በአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆኗን ገልጻለች። አትክልትና ፍራፍሬ ከመሸጥ ጎን ለጎን እንጀራ በመጋገርና በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኘች መሆኑንና ሥራዋን ለማስፋት ተግታ እየሠራች እንደምትገኝ ተናግራለች። ሌላዋ ወጣት ሸዋዬ ኃይሉ በበኩሏ፤ በተሰጣት የሥልጠና ድጋፍ የወረቀት ቦርሳ በማምረትና ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆኗን ገልጻለች። ከጓደኞቿ ጋር በመደራጀት የጀመረችው ሥራ በየወሩ እስከ 50 ሺህ ብር ገቢ እያስገኘላቸው መሆኑን አስረድታለች። በ2019 በጀት ዓመት ለ11 ሺህ 923 ሥራ አጥ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወደ ሥራ መገባቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።  
የህዳሴ ግድብ ለሱዳን አዲስ የኢኮኖሚ እድል የሚፈጥርና የቀጣናዊ ትስስር መንገድ የሚከፍት ነው-ዓለም አቀፍ የውሃ ኤክስፐርት ፕሮፌሰር ሰይፍ አል-ዲን ሀማድ
Aug 20, 2026 239
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለሱዳን በርካታ የኢኮኖሚና የልማት እድሎችን የሚያስገኝና የቀጣናዊ ትስስር መንገድን ይበልጥ የሚያሰፋ መሆኑን የቀድሞው የሱዳን የውሃ ሀብት ሚኒስትርና ዓለም አቀፍ የውሃ ኤክስፐርት ፕሮፌሰር ሰይፍ አል-ዲን ሀማድ ገለጹ። ፕሮፌሰር ሰይፍ አል-ዲን ሀማድ ከአል-ኒላይን የዜና ቻናል ''ሙቅረን አል-ኒላይን'' ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቃለ-መጠይቅ፤ በወንዝ ላይ በደረጃ (Cascade System) የሚገነቡ ግድቦች የተቀናጀና ዘመናዊ አስተዳደር ከተከተሉ፣የወንዙን የተፈጥሮ ፍሰት በማስተካከልና በማረጋጋት ለተፋሰሱ ሀገራት የጋራ ጥቅም የሚሰጡ እንጂ በምንም አይነት መልኩ ስጋት ሊሆኑ እንደማይችሉ አስረድተዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ የዓባይ ወንዝ በክረምት ወቅት ብቻ በከፍተኛ መጠን ይፈስ የነበረበትን ሁኔታ በመቀየር፣ዓመቱን ሙሉ የተስተካከለና የተመጣጠነ የውሃ ፍሰት እንዲኖር እንደሚያደርግ አመልክተዋል። ይህም ሁኔታ ለሱዳን በርካታ የኢኮኖሚና የልማት እድሎችን ይዞ እንደሚመጣ አንስተዋል። ከእነዚህ እድሎች መካከል አንዱ የኤሌክትሪክ ማመንጨት አቅምን ማሳደግ ሲሆን፣ የተስተካከለው የውሃ ፍሰት እንደ ሮዛሪስ እና ሴናር ያሉ የሱዳን ግድቦች ያለ ተጨማሪ ወጪና ህዝብ መፈናቀል ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲያመነጩ የሚያስችላቸው መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የወንዙ ውሃ ከፍ ማለቱ የሱዳን አባወራዎችና አምራቾች ለግብርና መስኖ ይጠቀሙበት የነበረውን የፓምፕ ወጪ ከ30 እስከ 50 በመቶ ያህል እንደሚቀንስ አስረድተዋል። በተጨማሪም የተስተካከለው የውሃ ፍሰት በሱዳን የውሃ ላይ ትራንስፖርትን እንደገና እንዲያሰራራ ትልቅ እድል እንደሚፈጥር ፕሮፌሰር ሀማድ ገልጸዋል። በሌላ በኩል፣ የሕዳሴው ግድብ ይፈርሳል ወይም የጎርፍ አደጋ ያመጣል በሚል የሚነሱ ስጋቶችን ፕሮፌሰር ሀማድ በሳይንሳዊ ማስረጃ ውድቅ አድርገውታል። ግድቡ ከምስራቅ አፍሪካ ስምጥ ሸለቆ የመሬት መንቀጥቀጥ ቀጠና 600 ኪሎ ሜትር ያህል የራቀ ከመሆኑም በላይ፣ በካሬ ሜትር እስከ 10 ሺህ ቶን መሸከም በሚችል ጠንካራ የግራናይት ድንጋይ ላይ የተገነባ በመሆኑ ምንም ዓይነት የመዋቅር አደጋ የለበትም ብለዋል። እንደ የቀድሞው የሱዳን የውሃ ሀብት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ሰይፍ አል-ዲን ሀማድ ገለጻ፤ ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ የምትገነባቸው አዳዲስ ግድቦች የውሃ አሞላልን አስመልክቶ ቅድመ ስምምነት ላይ ከተደረሰባቸው በሱዳን ላይ ምንም ዓይነት ስጋት አያመጡም። ፕሮፌሰር ሀማድ ሱዳን ከተሳሳቱ ስጋቶችና እርግጠኛ ካልሆኑ ሀሳቦች በመውጣት፣የሕዳሴ ግድብ የፈጠረው አዲስ የውሃ እውነታ ጋር የሚጣጣም ብሔራዊ የውሃ ሀብት ስትራቴጂ ማዘጋጀት እንዳለባት አሳስበዋል። ለዚህም በሀገሪቱ መሪ የሚመራ ብሔራዊ የውሃ ሀብት ምክር ቤት ስራውን አጠናክሮ በመቀጠል የተቀናጀ እቅድ ማውጣት እንዳለበት ጠቁመዋል።
በይርጋዓለም ከተማ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የዶሮ አርቢዎችን ኢኮኖሚያዊ አቅምን እያሳደገ ነው
Aug 19, 2026 283
ይርጋለም፤ ነሀሴ 13/2018 (ኢዜአ)፡-በይርጋዓለም ከተማ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዶሮ እርባታ ሥራ የተሰማሩ ማህበራት ከእንቁላል ምርታቸው ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን ገለጹ። በሲዳማ ክልል ማዕከላዊ ሲዳማ ዞን ይርጋዓለም ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው ማህበራት እንደገለጹት፣ የተሰማሩበት የዶሮ እርባታ ሥራ የእንቁላል ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የኢኮኖሚ አቅማቸውን እያሳደገው ነው። ከእንቁላል ሽያጭ በሚያገኙት ገቢ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱንም ለኢዜአ ገልጸዋል።   ‎በከተማው የጌዶሴይ ዶሮ እርባታ ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ከተማ ካቢሶ ሥራውን በ1 ሺህ የእንቁላል ጣይ ዶሮዎች እንደጀመሩ አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ያሏቸው የዶሮዎች ቁጥር 4 ሺህ መድረሱን ተናግረዋል። ከእነዚህም በቀን ከ3 ሺህ 700 በላይ እንቁላል እንደሚሰበስቡና ከሽያጩም የተሻለ ገቢ እያገኙ መሆናችውን አስረድተዋል።   ከእንቁላል ምርት ባለፈ የአንድ ቀን ጫጩቶችን በማስመጣትና አሳድገው በ48 ቀናቸው ለተጠቃሚዎች በማስረከብ ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በሥራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ከመንግስት የመስሪያ ቦታ፣ የስልጠናና ሌሎች ድጋፎችን እያገኙ ማግኘታቸውን ተናግረዋል።   የደረሰና ቤተሰቡ የዶሮ እርባታ ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ደረሰ አሰፋ በበኩላቸው "የዶሮ እርባታ ሥራ አስፈላጊ መኖና ሕክምናን ከማሟላት ባለፈ በጥንቃቄ መስራት ከተቻለ ትርፋማ ያደርጋል" ብለዋል። በአንድ ሺህ የእንቁላል ጣይ ዶሮዎች የጀመሩትን ሥራ አስፋፍተው በአሁኑ ወቅት ከ10ሺህ በላይ ዶሮዎች እንዳሏቸው ገልፀዋል፡፡ በቀን ከ9 ሺህ በላይ እንቁላል ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ደረሰ፣ በስራቸው ለሌሎቸም የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ነው የተናገሩት ከመንግስት ነጻ የዶሮ ክትባቶችን ጨምሮ የሙያና የተለያየ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑንም ገልፀዋል፡፡   የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ምክትልና የዝርያ ማሻሻልና መኖ ልማት ዘርፍ ኃላፊ አደገ አለሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው በክልሉ በሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር ከተከናወኑ ተግባራት መካከል የዶሮ ልማት ሥራ ትልቅ እመርታ ማሳየቱን ገልጸዋል፡፡ የዶሮ ሀብት ልማት በየቤታቸው የተወሰኑ ዶሮዎችን የሚያረቡ አርሶ አደሮች፣ በማህበር ተደራጅተው የሚሰሩ ዜጎችን እንዲሁም በግል የሚያለሙ ባለሀብቶችን ተጠቃሚ አድርጓል ብለዋል። በዘርፉ ለተሰማሩ ማህበራት እና ዶሮ ፈላጊዎች የዶሮ አቅርቦት፣ የሙያ እገዛና ሌሎች የድጋፍና ክትትል ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ኃላፊው አደገ (ዶ/ር) ጠቁመዋል፡፡ እንደእሳቸው ገለጻ ከአምስት ዓመት በፊት በክልሉ በዓመት ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን በታች የነበረውን የዶሮ ሥርጭት በአሁኑ ወቅት 20 ሚሊዮን ለማድረስ ተችሏል። በተያዘው 2019 በጀት ዓመትም 24 ሚሊዮን ዶሮዎችን ለማሰራጨት ማታቀዱን ጠቁመዋል፡፡    
በድሬደዋ በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተሰማሩ አልሚዎችን በመደገፍ የኮንፍረንስ ቱሪዝምን ማሳደግ ተችሏል
Aug 19, 2026 100
ድሬደዋ፤ ነሐሴ 13/2018(ኢዜአ)፦ በድሬደዋ ከተማ አስተዳደር በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተሰማሩ አልሚዎችን በመደገፍ የኮንፍረንስ ቱሪዝምን ማሳደግ መቻሉን የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ አመራር አካላት በሆቴል ኢንቨስትመንት ለመሰማራት ፈቃድ ወስደው ግንባታ ላይ የሚገኙ ባለኮከብ ሆቴሎችን የመስክ ጉብኝት አድርገዋል። ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ አስተዳደሩ የከተማዋን ኢንቨስትመንት ለማስፋፋት የቀየሰው የአሰራርና የህግ ማእቀፍ በርካታ አልሚዎችን ወደ ስራ ማስገባት አስችሏል። ለዚህም የመሠረተ ልማት፣ የመሬት አቅርቦት፣ የውሃ፣ የኤሌክትሪክ፣ የፋይናንስ እና ሌሎች ድጋፎችን ከመስጠት አኳያ ከተቋማት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል። ይህም በተለይም በሆቴሎች ዘርፍ ፈቃድ ወስደው በግንባታ ላይ የነበሩ አልሚዎች ስራቸውን አጠናቀው ወደ አገልግሎት በመግባት የቱሪዝሙን እንቅስቃሴ እያሳደጉ መሆናቸውን አስረድተዋል። ለአብነትም በበጀት አመቱ በግንባታ ላይ የነበሩ አምስት ሆቴሎች ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን አንስተዋል። ይህም ከተማዋን የቱሪዝም ኮንፍረንሰ ማእከል ለማድረግ የተጀመረውን ጥረት ለማሳካትና የቱሪስቶችን ቆይታ ለማራዘም ማገዙን ገልጸዋል ። የዛሬው ጉብኝትም አስተዳደሩ በሆቴል አገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩ ባለሃብቶችን ለማበረታታት ያለመ ነው ብለዋል። እንዲሁም በግንባታ ላይ ያሉ ሆቴሎችን በማበረታታት በፍጥነትና በጥራት ወደ አገልግሎት ለማስገባት አቅጣጫ ለማስቀመጥ መሆኑን ጠቅሰዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወንደሰን አባይ አስተዳደሩ ተፈጥሮአዊና ታሪካዊ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማት የዘርፉን ጠቀሜታ ለማጉላት እየሰራ ነው ብለዋል። በዚህም መስህቦቹን ለጎብኚዎች አመቺ የማድረግና ከከተማዋ ኮሪደር ልማት ጋር ተሰናስሎ እንዲሄድ መደረጉን ገልጸዋል። በከተማዋ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶችን ፍሰትና የቆይታ ጊዜ ለማራዘም የቱሪስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ማስፋፋት ላይ ትኩረት መሰጠቱን ጠቁመዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት አመት ከ700 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥ እና ከ15 ሺህ በላይ ቱሪስቶች መስህቦቹን መጎብኘታቸውን አስረድተዋል። የከተማዋ የቱሪዝም ልማትም የስራ እድልን ለማስፋትና የከተማውን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ከፍ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል። በተያዘው በጀት አመትም በቱሪዝም ዘርፍ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በግንባታ ላይ ከሚገኙ ባለኮኮብ ሆቴሎች ባለቤት አቶ ሱራፌል ሲሳይ በበኩላቸው የከተማ አስተዳደሩ ለዘርፉ የሚያደርገው ድጋፍና ክትትል ስራቸውን ለማቀላጠፍ እያገዛቸው መሆኑን ጠቅሰዋል። በግባታ ላይ የሚገኘው ሆቴልም ለከተማዋ የቱሪስት ፍሰትና ለወጣቶች የስራ ዕድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል።      
በአማራ ክልል የአፈር ለምነትን የሚያሻሽል የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል
Aug 19, 2026 116
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል በበጀት ዓመቱ የአፈር ለምነትን የሚያሻሽል 86 ሚሊዮን ሜትር ኩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደተግባር መገባቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የአፈር ለምነት ባለሙያ አቶ አምሳሉ አድማስ ለኢዜአ እንደገለጹት በአሲድ የተጠቃ አፈር ለምነትን ለመመለስና የሰብል ምርታማትን ለማሳደግ የተፈጥሮ ማዳበሪያን አዘጋጅቶ መጠቀም ጠቀሜታው የጎላ ነው።   ለዚህም በበጀት ዓመቱ ከ3 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚበልጡ አርሶ አደሮችን በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅት በማሳተፍ 86 ሚሊዮን ሜትር ኩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ግብ ተይዞ ወደተግባር ተገብቷል። ከቅጠላቅጠሎች፣ ከተረፈ ምርት፣ ከከብቶች እዳሪ፣ ከአመድና ለኮምፖስት ዝግጅት ጠቃሚ ከሆኑ ሌሎች ንጥረ ነገሮች ጥራቱን ጠብቆ እንዲዘጋጅ ለአርሶ አደሩ ሙያዊ ድጋፍ እየተሰጠ መሆኑንም ገልጸዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያ ሳይንሳዊ ሂደቱን ጠብቆ ከተዘጋጀ የአፈር ቅንጣትና ለምነት እንዲሻሻል፣ የሰብል ምርታማነት እንዲጨምር፣ አፈር በውስጡ ውሃን ለረጅም ጊዜ እንዲቋጥር የጎላ ጠቀሜታው እንዳለውም አመልክተዋል። በበጀት ዓመቱ የሚዘጋጀው የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለቀጣይ ዓመት መስኖና የመኽር እርሻ ጥቅም ላይ ለማዋል ከወዲሁ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በማዳበሪያ ዝግጅቱ እየተሳተፉ ካሉት መካከል በምዕራብ ጎጃም ዞን ቡሬ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ታደሰ አለሙ በሰጡት አስተያየት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማዘጋጀትና መጠቀም ከጀመሩ ከ15 ዓመት በላይ እንደሆናቸው ገልጸዋል። በተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘገጃጀት ላይ ከግብርና ባለሙያዎች ባገኙት የካበተ ልምድና ዕውቀት በዓመት እስከ 23 ሜትር ኩብ ኮምፖስት ማዳበሪያ በጥራት አዘጋጅተው እንደሚጠቀሙ ተናግረዋል። የሚያዘጋጁትን ኮምፖስት ማሳቸው ላይ በመጨመር የአፈር ለምነትን ከማሻሻል ባለፈ የሰብል ምርታማነትና ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን አመልክተዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘጋጅተው መጠቀም ከጀመሩ ወዲህ ለምነቱን አጥቶ ከምርት ውጭ ሆኖ የቆየ ግማሽ ሄክታር መሬት ለምነቱ መመለሱን የገለጹት ደግሞ በዞኑ የሰከላ ወረዳ አርሶ አደር ፈጠነ አስረስ ናቸው። ከዚህም በየዓመቱ እስከ 12 ኩንታል የስንዴና የገብስ ምርት በመሰብሰብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው፣ በተያዘው በጀት ዓመትም 18 ሜትር ኩብ ኮምፖስት በጥራት አዘጋጅተው ለመጠቀም ወደሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። የቢሮው መረጃ እንደሚያመለክተው በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተዘጋጀ ከ81 ሚሊዮን ሜትር ኩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለመስኖና ለመኸር ሰብል ልማት ጥቅም ላይ መዋሉ ታውቋል።  
በዞኖች ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Aug 19, 2026 118
ሆሳዕና ፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተከናወነ ያለው ተግባር ውጤታማ መሆኑን የጉራጌ፣ ስልጤና ከምባታ ዞኖች አስታወቁ። በስልጤ ዞን ግብርና መምሪያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከድር ሁሴን እንዳሉት፣ በዞኑ የማህበረሰቡን ተሳትፎ በማሳደግ ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተደረገ ባለው ጥረት ውጤት ተመዝግቧል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በራስ አቅም ሰብዓዊ ድጋፍን ለመሸፈን የሚውል የእህል ክምችት ለመያዝ በተከናወነ ተግባር፣ እስከ አሁን ከ11 ሺሕ 860 ኩንታል በላይ ምርት በወል መሬት ላይ አምርቶ ማከማቸት እንደተቻለ ገልጸዋል። በተጨማሪም ማህበረሰቡን በማሳተፍ 22 ሚሊዮን ብር በጥሬ ገንዘብና የተለያዩ ቁሳቁሶችን በማሰባሰብ ማከማቸት ተችሏል ብለዋል። በተያዘው የበጀት ዓመትም በዞኑ በመኸር ወቅት 207 ሄክታር ማሳ በበቆሎ ሰብል ለዚሁ ተግባር እየለማ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በተጨማሪም 30 ሚሊዮን ብር በማሰባሰብ ለሚከሰቱ ሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   በጉራጌ ዞን ግብርና መምሪያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጊዜወርቅ አለሙ በበኩላቸው፣ ለተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት በማህበረሰብ ተሳትፎ 6 ሺሕ 800 ኩንታል እህል ማከማቸት ተችሏል ብለዋል። በተያዘው የበጀት ዓመትም በዞኑ በመኸር ወቅት 260 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች የለማ ሲሆን ፣ ከ19 ሚሊዮን ብር በላይ የመጠባበቂያ ገንዘብ ለማሰባሰብ ግብ ተጥሎ ወደ ትግበራ መገባቱን አመልክተዋል።   በከምባታ ዞን ግብርና መምሪያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አስራት ማቲዎስ እንደገለጹት ደግሞ፣ በዞኑ በተለያዩ ምክንያቶች ለሚከሰቱ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ መስጠት እንዲቻል ከማህበረሰቡ ጋር ስምምነት ላይ ተደርሷል። በዚህም 480 ኩንታል የምግብ እህል ከማምረት ባሻገር፣ 22 ሚሊዮን ብር በጥሬ ገንዘብ መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። በመኸር እርሻም 180 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች እየለማ ሲሆን 124 ሚሊዮን ብር ለማሰባሰብ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ጠቁመዋል።    
ኢትዮጵያ ምርቶቿን በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ በማድረግ የወጪ ንግድ አቅሟን እያሳደገች ነው
Aug 19, 2026 346
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ምርቶቿን በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ በማድረግ የወጪ ንግድ አቅሟን እያሳደገች መሆኑን የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር በኢትዮጵያ ከሚገኘው የቻይና ኤምባሲ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የኢትዮጵያና የቻይናን ዘላቂና ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ወደ ላቀ የንግድና ኢኮኖሚ ትስስር የሚያሸጋግረውና የፕሮሞሽን ሥራዎች አካል የሆነ "Export to China" መድረክ በይፋ ተጀምሯል።   በመድረኩ የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፣ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ፣ የሁለቱ ሀገራት ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ አስመጪና ላኪዎች ታድመዋል። በመድረኩ የቻይና አስመጪዎች ጥራት ያላቸውን የኢትዮጵያ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በስፋት እንዲገዙ ለማድረግ የሚያስችል የፕሮሞሽን ሥራዎች ተከናውኗል። በዚህም ከ340 ሚሊዮን ዶላር በላይ ዋጋ ያላቸው 33 የንግድ ለንግድ (B2B) የግብይት ኮንትራቶች በቡና፣ ሰሊጥ፣ አኩሪ አተር፣ በጨርቃጨርቅ እና በማዕድን ዘርፎች ወደ ውጭ ለመላክ ተፈራርመዋል። የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት የስምምነቱ ዓላማ የኢትዮጵያን የወጪ ንግድ ገቢ ግኝት ለማሳደግ የሚያስችል የፕሮሞሽን ሥራዎችን በቻይና ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። ሚኒስቴሩ ከቻይና ኤምባሲ ጋር ሰፋፊ ውይይቶችን ሲያደርግ መቆየቱን ገልጸው፤ ስምምነቱ ከብዙ ሥራዎች በኋላ የተገኘ ውጤት መሆኑንም ገልጸዋል። 33 የሚጠጉ ስምምነቶች መፈረማቸውን ገልጸው፤ እነኝህም 340 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ሊያስገኙ የሚችሉ መሆኑን ጠቁመዋል። ስምምነቱን ወደ ትልቁ የቻይና ገበያ ለመግባት በቻይና መንግሥት የተቀረጸው ኢኒሼቲቭ አካል መሆኑን አንስተዋል። በቡና፣ በቅባት እህል፣ በጥራጥሬ፣ በቆዳ፣ በማዕድን ምርቶች እና በጨርቃ ጨርቅ ላይ ከስምምነት መደረሱን ተናግረዋል። ስምምነቱ ከቃል በዘለለ ተግባራዊ ውጤት የተገኘበት ስኬት መሆኑንም ገልጸዋል። መንግሥት በ2019 በጀት ዓመት ከወጪ ንግድ 13 ነጥብ 4 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት ማቀዱን ገልጸው፤ ስምምነቱ ይህንን ማሳካት የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። እንዲሁም የኢትዮጵያ ምርቶች በዓለም ገበያ የሚያስተዋውቅና ተወዳዳሪነታቸውን በማሳደግ የተያዘውን ውጥን የሚያሳካ መሆኑን አመላክተዋል። በቀጣዮቹ ጊዜያትም ከተለያዩ ሀገራት ጋር ምርቶችን በጥራት በዋጋ እና በብዛት ተወዳዳሪ ሆነው እንዲቀርቡ በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን ምርቶች በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ ማድረግ የሚያስችሉ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጠሉም እንዲሁ።   በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ በበኩላቸው የስምምነቱ ዓላማ ለሁሉም የወጪ ንግድ ትልቅ ገበያ ማግኘት መሆኑን ገልጸዋል። ቻይና በከፍተኛ ፍጥነት በማደግ ላይ እንደምትገኝ ገልጸው፤ የኢትዮጵያ እጅግ አያሌ ምርቶችና የበለጸጉ ተፈጥሯዊ ሀብቶችም እንዲሁ በፍጥነት በማደግ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በሁለቱ ገበያዎች እና ምርቶች መካከል ያለው ትስስር የሀገራቱን እድገት ለማፋጠን አስፈላጊ መሆናቸውንም አመላክተዋል። ስምምነቱ ቻይና ከአፍሪካ እና ከኢትዮጵያ ጋር የዜሮ ታሪፍ ፖሊሲ ከተቀበለች እና መተግበር ከጀመረች ወዲህ የተወሰደ ወሳኝ እርምጃ መሆኑን ጠቁመዋል።
በአማራ ክልል ኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን የመኸር እርሻ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል- መምሪያው
Aug 19, 2026 100
ደሴ፤ነሐሴ 13/2018( ኢዜአ):-በአማራ ክልል ኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን በመኸር ወቅት የሚከናወነው የአረምና ተባይ ቁጥጥር ሥራን በማጠናከር ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ደጀኔ ከበደ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በያዝነው መኸር በኩታ ገጠምና በመስመር በመዝራት እንዲሁም ግብአትን በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ይገኛል። በዚህም በ58 ሺህ 632 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራውን የሰብል ቡቃያ የአረምና የተባይ ቁጥጥር ሥራ እየተካሄደ መሆኑን አስረድተዋል። የተዘራውን ሰብል እስከ ሁለት ጊዜ በማረም ነጻ የማድረግና በየቀኑ ማሳውን በማሰስ ተባይን በመቆጣጠር ምርታማነቱን ለማሳደግ እየተሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ይህም የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያና ኢንዱስትሪ ግብአት ለማቅረብ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም አልፎ አልፎ የሚስተዋለውን የዝናብ መቆራረጥ ለመቋቋም አርሶ አደሩ በማሳው ዳርና ዳር ጉድጓዶችን በመቆፈር ውሃ የማሰባሰብ ስራ እንዲያከናውን ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ነው ብለዋል። በአርጠማ ፉርሲ ወረዳ የዲምቱ ጨቆርሶ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መሀመድ ከድር በሰጡት አስተያየት፣ በዘንድሮው መኸር ሁለት ሄክታር ማሳቸውን በማሽላ፣ ማሾና በሌሎችም ሰብሎች አልምተዋል። ሰብሉን ከአረም በማጽዳትና በየቀኑ የተባይ ቁጥጥርና አሰሳ በማካሔድ ከ40 ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ አልመው እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል። ሌላው የዳዋጨፋ ወረዳ የሸክላ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሰይድ አደም በበኩላቸው፣ በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ በመታገዝ ፈጥነው የሚደርሱና ምርታማ የሆኑ ሰብሎችን ማልማት መቻላቸውን ገልጸዋል። አንድ ሄክታር መሬታቸውን ማሽላና ጤፍ በኩታ ገጠም ማልማታቸውን ጠቁመው፣ የዝናብ መቆራረጡን ለመቋቋም ውሃ እያሰባሰቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በብሔረሰብ አስተዳደር ዞኑ በመኸር ከለማው መሬት ከአንድ ነጥብ ስድስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
ግብፅ ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ያላትን ተፈጥሯዊ መብት ልታከብር ይገባል - የጂኦፖለቲክስ ባለሙያ ኤልያስ ዐቢይ
Aug 19, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ግብፅ የአባይ ወንዝን "ለብቻዬ ልጠቀም" የሚል ጊዜው ያለፈበት እሳቤ በመተው፣ የናይል ወንዝ የ86 በመቶ የውሃ ድርሻ ያላትን ኢትዮጵያ ተፈጥሯዊ የመልማት መብት ዕውቅና ልትሰጥ እንደሚገባ የጂኦፖለቲክስ ባለሙያው ኤልያስ ዐቢይ ገለጹ። የጂኦፖለቲክስ ባለሙያውና ደራሲው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ 135 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን የዕለታዊ ሕይወታቸውና ሀገራዊ የልማት ህልውናቸው እነዚህን ወሳኝ የተፈጥሮ ሀብቶች መሠረት ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ግብፅ ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን እንዳትጠቀም ለማድረግ የምታደርገው ተደጋጋሚ ጥረት መልክአ-ምድራዊ እውነታንና የፍትሐዊ የውሃ አጠቃቀም መርሆዎችን ያላገናዘበ መሆኑንም አብራርተዋል።   ግብፅ ለፍትሐዊ የውሃ ሀብት አጠቃቀም መርሆዎች ተገዢ አለመሆኗን ጠቅሰው፤ ይህም የሚመነጨው የዓባይን ወንዝ በብቸኝነት "የእኔ ብቻ ነው" ከሚል ጊዜው ያለፈበትና ዘመኑን የማይመጥን እሳቤ እንደሆነ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በዓባይ፣ በባሮ-አኮቦ እና በተከዜ ተፋሰሶች አማካኝነት ከፍተኛ ድርሻ ቢኖራትም፤ ግብፅ ግን የቀጣናውን የጂኦፖለቲክስ ውጥረቶችና ዓለም አቀፍ ተፅዕኖዎችን መሣሪያ በማድረግ የኢትዮጵያን የልማት እንቅስቃሴዎችና የሃይድሮ-ኤሌክትሪክ ልማት ፕሮጀክቶችን ስታደናቅፍ ቆይታለች። እንደ ባለሙያው ገለጻ፣ ይህ ዓይነቱ የማደናቀፍ አካሄድ ከኢትዮጵያ የውሃ መሠረተ ልማት የሚገኘውን ግልጽ አካባቢያዊና ቴክኒካዊ ጥቅሞች ለረጅም ጊዜ ችላ ያለ ነው። ውሃ በኢትዮጵያ ቀዝቃዛና ጥልቅ ሸለቆዎች ውስጥ በመከማቸቱ በሰሃራ በረሃ በሚገኘው የናስር ሀይቅ ላይ በከፍተኛ ሙቀት ምክንያት የሚፈጠረውን ከፍተኛ የውሃ ትነትና መባከን እንደሚያስቀር ተናግረዋል። ከአስዋን ግድብ በስተጀርባ የሚገኘው የናስር ሀይቅ በዓለማችን እጅግ ሞቃታማ ከሆኑ አካባቢዎች አንዱ በሆነው በሰሃራ በረሃ ውስጥ ወደ 6,000 ካሬ ኪሎ ሜትር የሚጠጋ ቦታ እንደሚሸፍን አመልክተዋል። በከፍተኛ ሙቀት ምክንያት በዓመት ከ10 እስከ 15 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውኃ እንደሚባክንና ይህም ሙሉ በሙሉ የባሮ-አኮቦ ወንዝ ወደ ነጭ ዓባይ ከሚወስደው የውሃ መጠን ጋር እኩል መሆኑን ያስረዱት።   ከዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ጋር በተያያዘ የጨመረው የሙቀት መጠን ይህ የውሃ መባከን የበለጠ እንዲባባስ ማድረጉን ጠቅሰው፤ በዚህ ረገድም ኢትዮጵያ የውሃ ብክነትና ትነትን ከመቀነስ አንጻር ያላትን ሚና አጉልተው አሳይተዋል። የሀገሪቱን የወደፊት ስትራቴጂካዊ ጉዞ አስመልክቶ ኤልያስ እንደገለጹት፤ የውስጥ ጥንካሬ፣ ፈጣን ኢኮኖሚያዊ እድገትና ሀገራዊ አንድነት ለውጭ ጫናዎችና ተቃውሞዎች ኢትዮጵያ የምትሰጠው ዋናና ውጤታማ ምላሾች ናቸው። ሁሉን አቀፍ ልማትን ማፋጠን እና ሀገራዊ ውይይትን ማጎልበት ዘላቂ ሀገራዊ ግቦችን ለማሳካት ወሳኝ መሆኑንም አክለው ገልጸዋል። ይህም በበለጸገች ኢትዮጵያ አማካኝነት በአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ውስጥ ሰፊ የኢኮኖሚ ትስስርና ሰላም እንዲሰፍን አስተማማኝ መሠረት ይጥላል ብለዋል።
ከውጭ የሚገባውን የጥጥ ምርት በሀገር ውስጥ ለመተካት በተከናወኑ ተግባራት ውጤት እየተመዘገበ ነው
Aug 19, 2026 132
ጂንካ፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ከውጭ የሚገባውን የጥጥ ምርት በሀገር ውስጥ ለመተካት በተከናወኑ ተግባራት ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የጥጥ ምርት በስፋትና በጥራት ለማምረት የግል ባለሀብቱን ያሳተፈ ርብርብ እየተደረገ ይገኛል። በክልሉ ደቡብ ኦሞ ዞን በጥጥ ልማት ዘርፍ የተሰማሩ ባለሀብቶችን የስራ እንቅስቃሴን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ጎብኝተዋል። የቢሮ ኃላፊው በወቅቱ እንዳሉት፤ ከውጭ የሚገባውን የጥጥ ምርት በሀገር ውስጥ ለመተካት የተጀመረው ጥረት አበረታች ለውጥ እያመጣ ይገኛል። በክልሉ ጥጥን ጨምሮ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ የግብርና ምርቶችን ለማልማት የሚያስችል አቅም እንዳለም ተናግረዋል። የሀገር ውስጥ የጥጥ ምርትን ለማሳደግ የተጀመረውን ጥረት በማገዝ ረገድ የናሳ እርሻ ልማት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ልማታዊ ባለሀብቶችን በማበረታታት የሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት መሪ ተዋናይ እንዲሆኑ የክልሉ መንግስት የማያቋርጥ ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል። የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ በበኩላቸው፤ የደቡብ ኦሞ ዞን ለጥጥ እርሻ ልማት ተስማሚ የሆነ ስነ-ምህዳር ያለው በመሆኑ የግል ኢንቨስትመንቶች በጥጥ እርሻ ልማት ቢሰማሩ ውጤታማ እንደሚሆኑ ተናግረዋል። በጥጥ ልማት በመሳተፍ ላይ ከሚገኙ ኢንቨስተሮች የናሳ ብራይሌ እርሻ ልማት ለአካባቢው አርብቶ አደሮች ከሚፈጥረው የስራ ዕድል ባሻገር የቴክኖሎጂ ሽግግር በማድረግ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ዞኑ በዘርፉ መሰማራት ለሚፈልጉ ባለሀብቶች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም የመምሪያ ኃላፊው ጠቁመዋል። የናሳ ብራይሌ እርሻ ልማት በደቡብ ኦሞ ዞን በባና ፀማይ ወረዳ የወይጦ ወንዝን በመጥለፍ ከ2 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ጥጥ እያመረተ እንደሚገኝ የተናገሩት የእርሻ ልማቱ ስራ አስኪያጅ አቶ አረጋዊ ገብረስላሴ ናቸው። ድርጅቱ በዋናነት የሀገሪቱን የጥጥ ምርት ፍላጎት ሙሉ ለሙሉ ለመተካት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የእርሻ ልማቱ ለሀገር ውስጥ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች ጥሬ ዕቃ ከማቅረብ ባለፈ፣ በአካባቢው ባስገነባው የጥጥ መዳመጫ ፋብሪካ እሴት በመጨመር ወደ ውጭ ሀገራት በመላክ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እያስገኘ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በተጨማሪም ለ300 ቋሚ እና 3 ሺህ ለሚደርሱ የአካባቢው ነዋሪዎች ጊዜያዊ የስራ እድል መፍጠሩን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያዊያን በርካታ ግድቦችን የመገንባት አቅሙም ዝግጁነቱም አላቸው-አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር)
Aug 19, 2026 215
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያዊያን በርካታ ግድቦችን የመገንባት አቅሙም ዝግጁነቱም እንዳላቸው የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር) ተናገሩ። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት በዋናነት የግድቡን ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ በማስተባበር ግንባታው በስኬት እንዲጠናቀቅ ያደረገ ተቋም ነው። የጽሕፈት ቤቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር)፤ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የዓባይ ውሃ ፍትሃዊ አጠቃቀም ላይ ለዘመናት የቆየ የተዛባ አረዳድን የቀየረ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። ግድቡ የትኛውንም ሀገር እንደማይጎዳና ይልቁንም ቀጣናውን በኢነርጂ እያስተሳሰረ መሆኑ በተግባር መረጋገጡን ጠቅሰዋል። ነገር ግን ግብጽ ይህንን እውነታ በመካድ አሁን ላይ የቀደመ በጩኸት የማደናገር ተግባሯን በስፋት እያከናወነች መሆኑን ተናግረዋል። ዓባይ የተፋሰሱ ሀገራት በትብብር የሚጠቀሙት ሃብት እንጂ የግብጽ የግል ንብረት አይደለም ያሉት አረጋዊ (ዶ/ር)፤ከዚህ አኳያ የግብጽ የማደናገር ዘመቻ ሊቆም ይገባል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ ዋነኛ ዓላማ በትብብር ማደግ መሆኑንም አብራርተዋል። ኢትዮጵያዊያን በትብብር ምን ማሳካት እንደሚችሉ በታላቁ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ ማሳየታቸውን አንስተው፤ በቀጣይም በርካታ ግድብ የመገንባት አቅሙም ዝግጁነቱም አላቸው ብለዋል። በታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ወቅት ሕዝብን በማስተባበር ረገድ በርካታ ጠቃሚ ልምድ መገኘቱንም ተናግረዋል። ይህ ልምድ በቀጣይ ለሚከናወኑ መሰል የልማት ስራዎች ትልቅ ግብዓት መሆኑንም አብራርተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም