ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ኢትዮጵያ እንደ ሕዳሴ ግድብ ሁሉ የባሕር በር ጥያቄዋንም ማሳካት የምትችል ታላቅ ሀገር ናት - ኡስታዝ ጀማል በሽር
Aug 28, 2026 193
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ እንደ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ሁሉ የባሕር በር ጥያቄዋን ማሳካት የምትችል ታላቅ ሀገር መሆኗን የዓባይ ንጉሶች ሚዲያ ባለቤት ኡስታዝ ጀማል በሽር ተናገሩ። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ የውሃ ሀብቶቿን በራሷ አቅም አልምታ መጠቀም እንደምትችል ያሳየ መሆኑንም ገልጸዋል። ኡስታዝ ጀማል በሽር፤ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ቀጣናውን በኤሌክትሪክ ኃይል በማስተሳሰር ትብብርን ከማጠናከር አኳያ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከተፋሰሱ ሀገራት ጋር ያላት ትብብር በጋራ ተጠቃሚነትና ልማት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ታላቁ የህዳሴ ግድብ በተግባር ማሳየቱንም ነው የጠቆሙት። ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን እንዳትጠቀም የሚከለክላት ማንም አካል እንደሌለ ጠቅሰው የሀገሪቷ የመልማት መብት ዓለም አቀፍ ህጎችና መርሆዎችን ያከበረ እንደሆነም ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን ተጠቅማ በቀጣይ ለማከናወን ያሰበቻቸው ስራዎች ሀገሪቷን ወደ ተሻለ ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ናቸው ሲሉም ተናግረዋል። እየተጠናቀቁ ያሉ የመስኖ ግድቦች፣ አብዛኛው ስራ የተጠናቀቀው የኮይሻ ኤሌክትሪክ ማመንጫ ፕሮጀክትና ሌሎች ስራዎች የኢትዮጵያን የልማት ውጥን እውን የሚያደርጉ ናቸው ብለዋል። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ በሁሉም መስኮች ያሰበቻቸውን እያሳካች መሆኑን ጠቅሰው፤ በከተማ ልማት፤ ቱሪዝም እንዲሁም በምክክር የመግባባት ዴሞክራሲን በመገንባት ረገድ ውጤታማ ስራ እያከናወነች ስለመሆኑ አብራርተዋል። አሁን ደግሞ የኢትዮጵያ የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ የሆነውን የባሕር በር ጥያቄ በይፋ አንስታለች ነው ያሉት። የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ የህልውና ጉዳይ እና በፍትሃዊነት የመልማት ጥያቄ መሆኑን በማንሳት፤ ይህንን ማሳካት ደግሞ የትውልዱ የማይቀር እውነት ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ የባህር በር ማግኘቷ አይቀሬ መሆኑን ጠላት ሳይቀር እየመሰከረው ያለው ሃቅ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ እንደ ሕዳሴ ግድብ ሌሎች ታላላቅ ፕሮጀክቶች ሁሉ የባሕር በር ጥያቄዋንም ማሳካት የምትችል ታላቅ ሀገር ስለመሆኑም ኡስታዝ ጀማል ተናግረዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በመኸር እርሻው ከ72 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቅባት እህሎች እየለማ ነው
Aug 28, 2026 126
አምቦ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን በመኸር እርሻው ከ72 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቅባት እህሎች በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገልጿል። ምዕራብ ሸዋ ዞን ለተለያዩ የሰብል አይነቶች ተስማሚ የሆነ የአየር ንብረት እና ለም አፈር ያለው አካባቢ ነው። ዞኑ ከዋና ዋናዎቹ የጥራጥሬ እና የእህል ዘሮች ባሻገር፣ እንደ ኑግ፣ ተልባ፣ ሰሊጥ እና የጎመን ዘር ያሉ የቅባት እህሎችን በማምረት በኩል ከፍተኛ አቅም አለው። በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የአዝእርት ልማት ባለሙያ አቶ በላይ በቀለ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በ2018/19 የምርት ዘመን ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውን የቅባት እህሎች በማልማቱ ስራ ላይ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል። ከለማው ሰፊ መሬት ውስጥ 40 ሺህ 665 ሄክታሩ በሰሊጥ የተሸፈነ ሲሆን፣ ቀሪው መሬት ደግሞ በኑግ፣ በተልባ፣ በጎመን ዘር እና በለውዝ መልማቱን ባለሙያው ገልጸዋል። ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግም በግብርና ምርምር ማዕከላት የተሻሻሉ የቅባት እህሎች ለአርሶ አደሩ ተሰራጭተው ጥቅም ላይ እየዋሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። የቅባት እህል ልማቱ የምግብ ዘይት እጥረትን ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አቶ በላይ ተናግረዋል። በቅባት እህሎች ልማት 88 ሺህ 761 የዞኑ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ ሲሆን፣ አሁን እየለማ ካለው መሬት 653 ሺህ 535 ኩንታል ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ ጠቁመዋል። በልማቱ ከተሳተፉት መካከል የአምቦ ወረዳው አርሶ አደር ፈይሳ በቀለ በሰጡት አስተያየት፣ በግማሽ ሄክታር መሬት ላይ ኑግ እንዲሁም በሌላ ግማሽ ሄክታር ላይ ተልባ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል። ካለሙት መሬት ጥሩ ምርት እንደሚጠብቁ በመግለጽ፣ በአሁኑ ወቅትም ጠንካራ የአረምና የተባይ አሰሳ ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን አስረድተዋል። ሌላው የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር አለማየሁ በሬቻ፣ በመኸር እርሻው በግማሽ ሄክታር ማሳቸው ላይ ተልባና ጎመን ዘር መዝራታቸውን በመግለጽ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል። የቅባት እህል ምርት በገበያ ላይ ከፍተኛ ተፈላጊነት ያለው በመሆኑ፣ ልማቱን ይበልጥ የማስፋፋት እቅድ እንዳላቸው አስረድተዋል። አርሶ አደሮቹ በግብርና ባለሙያዎች አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገላቸው በመሆኑ፣ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። በምዕራብ ሸዋ ዞን ባለፈው መኸር ከለማው ከ69 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ከ623 ሺህ ኩንታል በላይ የቅባት እህል ምርት መገኘቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።
የህብረት ስራ ማህበራት ሪፎርም ለክልሉ ኢኮኖሚያዊ እድገት ወሳኝ ድርሻ አለው-ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር)
Aug 28, 2026 87
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል እየተከናወነ ያለው የህብረት ስራ ማህበራት ሪፎርም ለክልሉ አጠቃላይ ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና ለአምራቹ ተጠቃሚነት ወሳኝ ድርሻ እያበረከተ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) ገለጹ። በደቡብ ጎንደርና በምዕራብ ጎጃም ዞኖች ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሁለት የዘር ብዜትና ግብይት ህብረት ስራ ማህበራት ዩኒዮኖችን የማዋሃድ ስራ ዛሬ ተካሂዷል። የክላስተሩ አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ዩኒዮኖቹን ወደ አንድ የማዋሀድ ስራ የተካሄደው በሁሉም መስክ አቅም ፈጥረው የተጣለባቸውን ተልእኮ በተሻለ መልኩ እንዲወጡ ለማድረግ ነው። የጉና እና የዕድገት የዘር ብዜት የህብረት ስራ ማህበራት ዩኒየኖች መዋሃዳቸው ጠንካራ ኢኮኖሚያዊ አቅም በመፍጠር የአርሶ አደሩን የዘር አቅርቦት ችግር ለመፍታት የሚያስችል ነው ብለዋል። የተዋሃዱት ዩኒየኖች ‘‘አንድነት የዘር ብዜትና ግብይት ኃላፊነቱ የተወሰነ የህብረት ስራ ማህበራት ዩኒየን'' ተብለው የተቋቋሙ ሲሆን የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የጎላ ድርሻ ይኖራቸዋል ብለዋል። በተለይ ከበቆሎ ምርጥ ዘር በተጨማሪ የተለያዩ የሰብል ዘሮችን በጥራት አባዝተው ለአርሶ አደሩ እንዲያቀርቡ ድጋፍና ክትትል ይደረግላቸዋል ብለዋል። ባለፉት ሁለት ዓመታት በተካሄደ የሪፎርም ስራዎች 388 ሁለገብ ህብረት ስራ ማህበራትን 141 ሆነው እንዲዋሃዱ በማድረግ ፋይናንሻል አቅማቸውና የአመራር ብቃታቸውን ጠንካራ እንዲሆን ተደርጓል ያሉት ደግሞ የክልሉ ህብረት ስራ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጌትነት አማረ ናቸው። እንዲሁም 19 የህብረት ስራ ማህበራት ዪኒየኖችን ወደ 9 ዩኔዮኖች እንዲዋሃዱ በማድረግ የፋይናንስ አቅማቸው እንዲጠናከርና በገበያ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የማድረግ ስራ መከናወኑን ኮምሽነሩ አመልክተዋል። በዛሬው ዕለትም በዘር ብዜት ተሰማርተው ሲሰሩ የቆዩትን የ''ጉናና የዕድገት ዘር ብዜትና ግብይት ህብረት ስራ ማህበራት ዩኒየኖች' ውህደት መፈፀማቸው ለዘርፉ ዕድገት ወሳኝ ድርሻ እንዳለው አመላክተዋል። በቀጣይም ኮሚሽኑ ሌሎች ህብረት ስራ ማህበራትና ዩኒዮኖችን በማሰባሰብ ጠንካራ ሆነው እንዲወጡ የሪፎርም ስራውን አጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት። የአንድነት የዘር ብዜትና ግብይት ህብረት ስራ ማህበራት ዩኒዮን የቦርድ ሰብሳቢ አርሶ አደር ደሴ ተረፈ፤ ውህደቱ አሰራርን በማዘመንና ምርትና አገልግሎታቸውን ተደራሽ በማድረግ የአርሶ አደርን ተጠቃሚነት የሚያሳድግ ነው ብለዋል። በቀጣይም በክልሉ ከ32 ሺህ የሚበልጡ ህብረት ስራ ማህበራትንና 61 ዩኒዮኖችን ለማዋሃድ እንደሚሰራም ነው የጠቀሱት።
የአፍሪካን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠን የድንበር ላይ አሰራሮችን የሚያሳልጥ ተጨባጭ እርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል - የአፍሪካ ሕብረት
Aug 28, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠን የሀገራትን የድንበር ላይ አሰራሮችን የሚያሳልጥ ተጨባጭ እርምጃ መውሰድ እንደሚያስፈልግ የአፍሪካ ሕብረት ገለጸ። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽንና የዓለም ባንክ ያተዘጋጁ''አፍሪካን ማቀናጀት፤ ከተበታተኑ ትስስሮች ወደ ኢኮኖሚያዊ ማዕከላት'' የተሰኘ አዲስ አህጉራዊ የጥናት ሪፖርት ይፋ ሆኗል። የጥናት ሪፖርቱም የአፍሪካን ከቀረጥ ነፃ የንግድና የምርት ትስስር በማጠናከር የአህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣናን በዘመናዊ መሠረተ ልማት በማስደገፍ የአህጉሪቱን ኢኮኖሚ ውህደት ማጠናከር እንደሚገባ አመላክቷል። በሕብረቱ ኮሚሽን የኢኮኖሚ ልማት፣ ንግድ፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪና ማዕድን ኮሚሽነር ፍራንሲስካ ታቾፕ ቤሎቤ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ አፍሪካ በተሰናሰለ አሠራርና መሠረተ ልማት የሚመራ የኢኮኖሚ ውህደትን ማሳለጥ ያስፈልጋታል። ይህም የአህጉሪቱን የተበታተነ የገበያና የግብይት ሥርዓት ውጤታማነት በማሻሻል አፍሪካን የጠንካራ ኢኮኖሚ ማዕከል ለማድረግ ቁልፍ ሚና እንደሚኖረው ገልጸዋል። የአፍሪካ ኢኮኖሚ ውህደት በሚፈረሙ ስምምነቶች ብቻ አይሳካም ያሉት ኮሚሽነሩ፤ የአህጉሪቱን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠንም የሀገራትን የድንበር አሠራሮችን የሚያሳልጥ እርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል ብለዋል። የአፍሪካን አህጉራዊ የነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት የትብብር ማዕቀፍ በውጤታማነት በመተግበር የአህጉሪቷን ዜጎች የጋራ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ንግድና ኢንቨስትመንትን ማፋጠን እንደሚገባ ተናግረዋል። ለዚህም የአህጉሪቷን አባል ሀገራት የድንበር ላይ መተላለፊያ፣ ጉምሩክ፣ ታሪፍና የዲጂታል ክፍያ እንቅፋቶችን ማስወገድ የሚያስችል ቀልጣፋ አሠራር መዘርጋት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። የአህጉሪቷን የኢኮኖሚ ውህደትን ለማሳለጥ የሚደረጉ ጥረቶችም ጥሬ ዕቃን ከመላክ የተላቀቀ የኢንዱስትሪ፣ የኃይልና የትራንስፖርት እሴት ሰንሰለት የሚያጎለብት ነው ብለዋል። ይህም የበለፀገችና የተሳሰረች አፍሪካን የመገንባት የአጀንዳ 2063 ራዕይን በማሳካት የአፍሪካዊያንን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያሻሽል የኢኮኖሚ ምኅዳር መፍጠር እንደሚያስችል ገልጸዋል። የዓለም ባንክ የምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ ቀጣናዊ ምክትል ፕሬዝዳንት ንዲያሜ ዲዮፕ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአፍሪካ የተቀናጀ መሠረተ ልማትና የሎጂስቲክስ ሥርዓት ለኢኮኖሚ ውህደት አስፈላጊ ነው ብለዋል። የአህጉሪቷን የኢኮኖሚ ውህደት ለሚያሳልጥም የተቀናጀ የመሠረተ ልማት አቅርቦትን በመገንባት የአርሶ አደሩን፣ የኢንዱስትሪና ገበያን በቀጥታ የሚያገናኝ ምኅዳር መፍጠር እንደሚገባ ገልጸዋል። የመሠረተ ልማቶች ትስስር አህጉራዊ የግብርና ገበያዎችንና የፋብሪካ ምርቶችን በማጠናከር ለአፍሪካውያን ሰፊና ዘላቂ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥርም ጠቅሰዋል። የዓለም ባንክ የንግድ እንቅፋቶችን በመቀነስ፣ የድንበር ተሻጋሪ አሠራሮችን በማቃለል የአፍሪካን እውነተኛ የኢኮኖሚ ውህደትና የሥራ ዕድል በሚፈጥሩ መሠረተ ልማቶች ላይ ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
በዞኑ 217 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ለምቷል
Aug 28, 2026 60
ገንዳ ውኃ፣ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን በ217 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውል የአኩሪ አተር ሰብል እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተያዘው የመኸር ወቅት የኢንዱስትሪ ጥሬ ዕቃ ፍላጎትን ለማሟላትና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። የግብርናው ዘርፍ ለኢኮኖሚ እድገት ያለውን የጎላ አበርክቶ ለማሳደግ ምርታማነትን መጨመር አስፈላጊ በመሆኑ፣ በቂ የግብርና ግብዓት ለአርሶ አደሩ በወቅቱ እንዲሰራጭ መደረጉንም ተናግረዋል። በአኩሪ አተር ልማቱ 60 ሺህ የሚደርሱ አርሶ አደሮችና ከ600 በላይ አልሚ ባለሃብቶች የተሳተፉ ሲሆን፤ ከልማቱ ከ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ አስረድተዋል። ጥራቱ የተጠበቀ ምርት ለማግኘት ከዘር ወቅት ጀምሮ በቅድመና ድህረ-ምርት አያያዝ ላይ ሰፊ ክትትልና ቁጥጥር የማድረግ ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ኃላፊው አመልክተዋል። የምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ገብሬ መልኬ በበኩላቸው፤ በተያዘው የመኸር ወቅት ከ60 ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ማልማት መቻላቸውን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪዎች መስፋፋትና የገበያ ሁኔታው መሻሻል ለአኩሪ አተር ሰብል ልማት ይልጥ ትኩረት እንዲሰጡ እንዳደረጋቸውም ተናግረዋል። በወረዳው የኮረደም እርሻ ጣቢያ አልሚ አርሶ አደር ምህረቴ ምኒልክ፤ ምርታማነትን በሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎች በመታገዝ አኩሪ አተር እያለሙ መሆኑን ገልጸዋል። ከግብርና ባለሙያዎች የሚደረግላቸው ሙያዊ ድጋፍና የሚቀርቡ የግብርና ግብዓቶች የሰብሉ ቡቃያ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንዲገኝ ማስቻሉንም አክለዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን ባለፈው የምርት ዘመን ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ለምቶ 5 ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ምርት መገኘቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የታይላንድ–አፍሪካ ኢኒሼቲቭ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ትብብርን ለማጠናከር አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው
Aug 28, 2026 158
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ የታይላንድ–አፍሪካ ኢኒሼቲቭ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ትብብርን ለማጠናከር አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው ሲሉ የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉአንግኬትኬኦ ገለጹ። የታይላንድ-አፍሪካ የትብብር መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉአንግኬትኬኦ በመድረኩ ላይ ባደረጉት ንግግር ታይላንድ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ሁለንተናዊ ግንኙነት ወደ ላቀ የስትራቴጂያዊ አጋርነት ለማሳደግ የሚያስችል አዲስ ማዕቀፍ ይፋ አድርገዋል። ሚኒስትሩ በዚሁ መድረክ ላይ የጉብኝታቸው ዋነኛ መነሻ ኢትዮጵያ እና ናይጄሪያ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በአራት ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ የተመሰረተው ይህ የትብብር ማዕቀፍ በተለይም ከአፍሪካ ኅብረት እና ከምዕራብ አፍሪካ ሀገራት የኢኮኖሚ ማህበረሰብ (ECOWAS) ጋር ያለውን ተቋማዊ ትብብር በይበልጥ ለማጠናከር ያለመ ነው። በተጨማሪም በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና እና በደቡብ ምሥራቅ እስያ ሀገራት ማኅበር (ASEAN) መካከል ጠንካራ የኢኮኖሚ ድልድይ ለመፍጠር ታስቧል። ዓላማውን ከዳር ለማድረስም የታይላንድ የንግድ ልዑክ በአዲስ አበባ ከኢትዮጵያ የመንግሥት እና የግል ዘርፍ ተወካዮች ጋር በመገናኘት የንግድ ማኅበረሰቡን የሚያስተሳስር ውይይት እንደሚያደርግ ተገልጿል። በሌላ በኩል ታይላንድ የደቡብ-ደቡብ ትብብርን ለማጎልበት ለቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት የሚተገበር እና ሦስት ሚሊዮን ዶላር በጀት የተመደበለት አዲስ የድርጊት መርሐ ግብር ይፋ አድርጋለች። መርሐ ግብሩ በዋናነት በግብርና፣ በምግብ ዋስትና እና በቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ ትኩረት የሚያደርግ ሲሆን፣ በተለያዩ የአፍሪካ አካባቢዎች የግብርና ማሠልጠኛ ማዕከላትን ለማቋቋም ይውላል። በፈረንጆቹ 2028 የደቡብ ምሥራቅ እስያ ሀገራት ማኅበር ሊቀመንበርነትን የምትረከበው ታይላንድ፣ በማኅበሩ እና በአፍሪካ ኅብረት መካከል በምግብ እና ኃይል ዋስትና እንዲሁም በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ዙሪያ ያለውን ዘርፈ ብዙ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር እንደምትሠራ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አረጋግጠዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርናን በማዘመን የተገኙ ስኬቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Aug 28, 2026 78
ዱራሜ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርናን በማዘመን የተገኙ ስኬቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ ። "የተቀናጀ የግብርና ትጋት ለተመጣጠነ ምርታማነት" በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ ክልላዊ የግብርና ሴክተር የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና የ2019 ዕቅድ ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በዱራሜ ከተማ ተካሂዷል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኡስማን ስሩር በዚህ ወቅት እንዳሉት በክልሉ ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰሩ ሥራዎች ስኬት ተመዝግቧል። የዘርፉን ስኬታማነት ይበልጥ ለማሳደግ ለቴክኖሎጂና ለሰው ሀይል ልማት ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ መቻሉንም ጠቁመዋል። ይህም የአርሶ አደሩን የምግብ ሉአላዊነትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ ባለፈ ገበያን ለማረጋጋት እያገዘ በመሆኑ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል። የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ አበራ ወንድሙ በበኩላቸው በዞኑ ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተሰራው ሥራ ውጤት አስገኝቷል። አርሶ አደሩ በኩታ ገጠም የማልማት ልምዱን ከማስፋፋት ባለፈ የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀሙ ማደጉ በበቆሎ ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግ መቻሉን አስረድተዋል። በዘርፉ እየተመዘገቡ የሚገኙ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል የአመራሩ፣ የግብርና ባለሙያውን እና የአርሶ አደሩ ቅንጅታዊ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አቶ አበራ ገልጸዋል። የከምባታ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ ተሾመ ሄራሞ በበኩላቸው በዞኑ ከሰብል ልማት በተጨማሪ የቡና እና የቅመማ ቅመም ልማት እየተስፋፋ ነው። ለአብነትም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ12ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ዝንጅብል መልማቱንና ለአርሶ አደሩም የገበያ ትስስር መፈጠሩን አንስተዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርት በማምረት ሚናቸው እያደገ መጥቷል
Aug 28, 2026 85
አርባ ምንጭ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርት በማምረት ያላቸው ሚና እያደገ መምጣቱ ተገለጸ። "የኢትዮጵያን ይግዙ" በሚል መሪ ሃሳብ ክልል አቀፍ የንግድ ባዛር እና ኤግዚቢሽን ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ ተከፍቷል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ አቶ ተፈሪ አባተ እንደገለጹት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን ተከትሎ በክልሉ የሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርቶችን በማምረት በኩል ያላቸው ሚና እያደገ መጥቷል። በክልሉ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄና በገጠር ኢንዱስትሪያላይዜሽን የተቀናጀ ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፣ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ለማጠናከር የኤክስፖርት ምርት አቅርቦትን በጥራትና በብዛት ማሳደግ እንደሚገባ ጠቁመዋል። የክልሉ መንግስት የአምራች ኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ማነቆ የሆኑ ችግሮችን በመፍታት የተሻለ እመርታ ለማስመዝገብ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሠራ መሆኑንም ተናግረዋል። ህጋዊ የንግድ ስርአትና ተወዳዳሪነትን በማስፈን የክልሉን ኢኮኖሚ ለማረጋጋት በተደረጉ ጥረቶች ለውጥ እየተመዘገበ መሆኑንም አቶ ተፈሪ አስረድተዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም የሀገር ውስጥ እና የውጭ ገበያ ድርሻን ከማላቅ ባለፈ ህገ-ወጥነትን በመከላከል ጤናማ የገበያ ሰንሰለት ለመፍጠር ትኩረት መሰጠቱን አቶ ተፈሪ አስታውቀዋል። የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ሃላፊ ሰናይት ሰለሞን በበኩላቸው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዋና ዋና ሀገራዊ ተልዕኮዎች የተሻለ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል። በተለይ 22 መካከለኛ እና 134 አነስተኛ ኢንዱስትሪዎች በሙሉ አቅም ማምረት እንዲችሉ መደረጉ ክልላዊ የማምረት አቅምን 63 በመቶ አድርሷል ብለዋል። በክልሉ የሚገኙ ከፍተኛ፣ መካከለኛና አነስተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ከውጭ ምርቶች ጥገኝነት የሚያላቅቁ ተኪ ምርቶችን በስፋት ማምረት እንደቻሉም ገልጸዋል። በክልሉ በሚገኙ 105 የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች የግብርና፣ የእንስሳትና እንስሳት ተዋጽኦ እንዲሁም የኢንዱስትሪ ምርቶች አቅርቦትን በማሻሻል የገበያ ማረጋጋት ሥራ ተሠርቷል ብለዋል። የአርባ ምንጭ "ኤሊያና ጋርሜንት" ምክትል ሥራ አስኪያጅ ኤርሚያስ ደማ እና በወላይታ ሶዶ "ሰላሙ የቆዳና የቆዳ ውጤቶች ማህበር" ሰብሳቢ ዮናስ ቶማስ በንግድ ባዛርና ኤግዚቪሽኑ መሳተፋቸው ምርቶቻቸውን በማስተዋወቅ የገበያ ሰንሰለት ለመፍጠር ምቹ አጋጣሚ ይፈጥራል ብለዋል። የሀገር ውስጥ ምርቶች በጥራትም ሆነ በንድፍ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እየሆኑ በመምጣታቸው ማህበረሰቡ የሀገሩን ምርት የመጠቀም ልምዱን ማሳደግ እንዳለበት አመልክቷል። ክልል አቀፍ የንግድ ባዛርና ኤግዚቢሽኑ ከዛሬ ጀምሮ ለተከታታይ ስድስት ቀናት የሚቆይ ሲሆን የተለያዩ አምራቾች፣ አስመጪዎች፣ ላኪዎች እና ኢንዱስትሪያሊስቶች ምርቶቻቸውን በማቅረብ እየተሳተፉ ነው።
በምስራቅ ወለጋ ዞን የክረምት እርሻ እና የልማት ኢንሼቲቮች አፈጻጸም በጥሩ ደረጃ ላይ ይገኛል
Aug 28, 2026 89
ነቀምቴ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ) :-በምስራቅ ወለጋ ዞን የ2018/2019 የምርት ዘመን የክረምት እርሻ እናየልማት ኢንሼቲቮች አፈጻጸም በጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት ምክትል ሀላፊ ደረጄ ብርሃኑ(ዶ/ር) በምርት ዘመኑ የተሻለ ምርት ለማግኘት ከአቅርቦት ጀምሮ በተሰራ ስራ ከታቀደው በላይ ማሳ በዘር ተሸፍኖ የሰብል እንክብካቤ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በዚህም 801 ሺህ 185 ሄክታር መሬት ለማረስ ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ 831 ሺህ 816 ሄክታር በማረስ ከታቀደው በላይ 103.8 በመቶ ማሳካት መቻሉን ያሳያል። አርሶ አደሩ የግብርና ፓኬጆችን በመጠቀም ምርታማነቱን እንዲያሳድግ በተጀመረው የሙሉ ፓኬጅ ስራም፤ 210 ሺህ 635 ሄክታር በሙሉ ፓኬጁ ማረስ መቻሉን ጠቁመዋል። በልማት ኢኒሼቲቭ በተከናወኑ የክረምት ሰብሎች ስራም በቆሎ 134 በመቶ፣ ቦሎቄ 122 በመቶ፣ ኦቾሎኒ 106 በመቶ፣ እንዲሁም ማሽላና ስንዴ እያንዳንዳቸው 103 በመቶ በማረስ ከዕቅድ በላይ መፈጸም ተችሏል ብለዋል። በሚገኘው የተሻለ ምርትም የራስ ፍጆታን ከመሸፈን ባለፈ ምርቱን ለማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ መታቀዱን ገልጸዋል። በኩታገጠም እርሻም 642 ሺህ 62 ሄክታር መሬት ታርሶ በዘር መሸፈኑን አስታውሰው፤ በዘርፉ በየጊዜው በተሰራው የግንዛቤ ማስጨበጫ እና በተደረገው የቅርብ ክትትል ለውጥ መመዝገቡንም አብራርተዋል። በሌላ በኩል ከግብርና ግብዓቶች አቅርቦት ጋር ተያይዞ፣ ወቅቱን የጠበቀ የዘር እና የማዳበሪያ አቅርቦት ለተጠቃሚዎች እንዲደርስ መሰራቱን ዶክተር ደረጄ ገልጸዋል። የተዘራው ሰብል ለተፈለገው ምርታማነት እንዲበቃና ከአረም ጥቃት እንዲጠበቅ የአረም መድኃኒት አቅርቦት እና አጠቃቀም ላይ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም ዶክተር ደረጄ አክለው ገልጸዋል። በተመሳሳይ በሰብል ጥበቃ በተለይም ተባይ ቁጥጥርም 226 ሺህ 326 ሄክታር ተፈትሾ 42 ሺህ 823 ሄክታር ላይ የመቆጣጠር ሥራ ተከናውኗል ብለዋል። በዞኑ የልማቱ ተሳታፊ አርሶ አደሮች በበኩላቸው የግብርና እና ሌሎች የልማት ኢንሼቲቮችን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ተግተው እየሰሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በዞኑ የዲጋ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ሰንበቶ ኢቲቻ በኩታገጠም እርሻ የተለያዩ ሰብሎችን እያለሙ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ባላቸው ከሁለት በላይ ሄክታር መሬትም የተሻለ ምርት ለማግኘት የግብርና ሜካናይዜሽኖችን እየተጠቀሙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሌላኛው አርሶ አደር አዲሱ ግዛው በየደረጃው የሚገኙ የግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ እና ክትትል እያደረጉላቸው እንደሚገኙ ተናግረዋል። ከራሳቸው ጥረት ጋር በባለሙያዎቹ በመታገዝም የተሻለ ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውን ገልጸዋል።
ተግባራዊ የተደረጉ የግብርና ቴክኖሎጂና የምርጥ ዘር አቅርቦቶች የአርሶ አደሩን ውጤታማነት እያሳደጉ ናቸው
Aug 28, 2026 230
ሮቤ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡- ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ተግባራዊ የተደረጉ የግብርና ቴክኖሎጂና የምርጥ ዘር አቅርቦቶች የአርሶ አደሩን ውጤታማነት እያሳደጉ መምጣታቸውን ምሁራን ገለጹ። መንግስት የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ ግብርናውን ከማዘመን ባለፈ ወቅትን ጠብቆ ብቻ ከማምረት ልምድ ለማውጣት የበጋ መስኖ ስንዴ ልማትን ተግባራዊ አድርጓል። ይህም የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ተረጂነትን ከማስቀረት ባለፈ የስንዴ ምርትን ወደ ውጭ በመላክ በኩል ከፍተኛ አስተዋጾ እያደረገ ይገኛል። ኢዜአ በመንግስት የግብርና ልማት እቅዶች ትግበራና ውጤታማነት ላይ ከዘርፉ ባለሙያዎችና ተመራማሪዎች ጋር ቆይታ አድርጓል። ሞያዊ ማብራሪያ ከሰጡ የዘርፉ ባለሙያዎች መካከል የብሔራዊ የስንዴ ምርምር ፕሮግራም አስተባባሪና የቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል ተመራማሪ ነጋሽ ገለታ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ የግብርና ልማት ትግበራ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን የመጠቀምና ወቅትን ጠብቆ ከማምረት ልምድ ለመውጣት የሚያስችል ነው። የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር የውኃ አማራጮችን ጥቅም ላይ በማዋል አርሶ አደሩ ዝናብን ብቻ ከመጠበቅ ወጥቶ የመስኖ ልማትን በስፋት በመጠቀም ምርታማነትና ተጠቃሚነቱን እያሳደገ መምጣቱንም ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት የግብርና ልማቱን ውጤታማ እንዲሆን የአፈር ለምነትን ለማሳደግና እርጥበትን ተጠቅሞ ለማልማት የተደረጉ ጥረቶች ስኬት ማስገኘታቸውንም አንስተዋል። በክልሉ ምርጥ ዘሮችን ከመጠቀም በተጨማሪ የኩታገጠም እርሻን ማስፋፋት የአርሶ አደሩን ምርታማነት ማሳደጉን የገለጹት ደግሞ የኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ የባሌ ቅርንጫፍ የአግሮኖሚ ከፍተኛ ባለሙያ አቶ ደሳለኝ ደጀኔ ናቸው። ለዚህም ኢንተርፕራይዙ የስንዴ፣ የገብስና የባቄላ ምርጥ ዘሮችን ለአርሶ አደሩ ከማቅረብ ባለፈ በኩታገጠም አሰራር እና በሰብል እንክብካቤ ላይ ሙያዊ ድጋፍ ማድረጉን አንስተዋል። በምርጥ ዘር አቅርቦቱ በሽታንና ድርቅን የሚቋቋሙ ሰብሎችን ለአርሶ አደሩ በማቅረብ የኢኮኖሚ አቅማቸውን ለማሳደግ የድርሻውን እየተወጣ መሆኑንም አስረድተዋል። በተለይም ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የምርጥ ዘር አቅርቦት በበቂ ሁኔታ ተደራሽ በማድረግ ውጤታማነት ለማሳደግ መሰራቱን አመልክተዋል። በመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የስንዴ ምርምር ፕሮጀክት ዋና አስተባባሪና ተመራማሪ ረዳት ፕሮፌሰር ጀማል አብዱልከሪም በበኩላቸው እንደገለጹት፤ ዩኒቨርሲቲው የመስኖ ስንዴን ልማትን ለማሳደግ አርሶ አደሮችን በሥልጠናና በግብዓት እያገዘ ነው። በተለይም ለባሌ፣ ለምሥራቅ ባሌና ለምዕራብ አርሲ ዞን አርሶ አደሮች ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም እውቀት እንዲያገኙ ስልጠና መሰጠቱን አስረድተዋል። የግብርና ቴክኖሎጂና የምርጥ ዘር አቅርቦቶች ተደራሽ በማድረግ የአርሶ አደሩን ውጤታማነት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ምርታማነትን በማሳደግ ተጠቃሚ እያደረጉ መሆኑንም አስታውቀዋል።
ግብፅ በዓባይ ወንዝ ምንም ዓይነት የውሃ ምንጭ አበርክቶ ሳይኖራት በኢትዮጵያ ላይ የምታቀርበው መሠረተ ቢስ ክስ ተቀባይነት የለውም
Aug 28, 2026 119
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ግብፅ በዓባይ ወንዝ ምንም ዓይነት የውሃ ምንጭ አበርክቶ ሳይኖራት በኢትዮጵያ ላይ የምታቀርበው መሠረተ ቢስ ክስ ፍጹም ተቀባይነት እንደሌለው የውሃ ሀብት ተመራማሪ ያዕቆብ አርሳኖ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያ የተቸራትን የተፈጥሮ ጸጋዎች እንዳትጠቀም የዘመናት ታሪካዊ ጠላት የሆነችው ግብፅ የውስጥ ባንዳዎችን በመቅጠር ጭምር ከልማትና ዕድገቷ ስትጎትታት መቆየቷ የሺህ ዘመናት የአደባባይ ሐቅ ነው። በዚህ ታሪካዊ ሸፍጥ ቁጭት የገባቸው ኢትዮጵያውያንም ከዓድዋ ጀግኖች የተረከቡትን የጀግንነት ወኔ በመላበስ ታላቁን የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በጉባ ተራሮች ግርጌ ዓባይን በማቀብ ብርሃንን ፈንጥቀዋል። ይህም ዓባይ “ግንድ ይዞ ይዞራል” የተባለለትን የዘመናት ተረትም በመቀየር ሕዳሴ ግድብ የሚያመነጨው ብርሃን ከሀገር የተሻገረ ግዙፍ የኤሌክትሪክ ኃይል በመፍጠር ቀጣናዊ የኢኮኖሚ በረከትን ፈጥሯል። በሕዳሴ ግድብ የተፈጠረው ቀጣናዊ የኃይል ትስስርም የኢትዮጵያን በጋራ የማደግ ቀጣናዊና አፍሪካዊ ራዕይን በአደባባይ የገለጠ አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደት ትልም ሆኖ ተመዝግቧል። የውሃ ሃብት ተመራማሪው ያዕቆብ አርሳኖ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ግብፅ በዓባይ ወንዝ ላይ የምታራምደው የሺህ ዘመናት ወንዙን በብቸኝነት የመጠቀም ግትር አቋም ከራስ ወዳድነት የሚመነጭ ስሁት ትርክት ነው። የሕዳሴ ግድብም የታችኞቹ ተፋሰስ ሀገራትን የደለል ክምችት፣ የጎርፍና የድርቅ አደጋ በመቀነስ እንዲሁም የሀገር ውስጥና ቀጣናዊ የኃይል አቅርቦት ትስስርን በማጠናከር ዘርፈ ብዙ በረከትእያስገኘ ነው ብለዋል። ግብፅ የዓባይን በብቸኝነት የመጠቀም ስግብግብ ፍላጎቷ የሺህ ዘመናት ትርክት መሆኑን አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅትም የግብፅ የፖለቲካ ልሂቃን በቅኝ ግዛት ዘመን ስምምነቶች በመቸንከር ዓባይን በብቸኝነት የመጠቀም ፍላጎትና ሕዳሴ ግድብ ላይ ስሁት ትርክታቸውን በመንዛት ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ኢትዮጵያም ሕዝቦቿን በማስተባበር በዓለም አቀፍ ሕግና መርህ በሳይንሳዊ መንገድ ሕዳሴ ግድብን በመገንባት ፍትሐዊ የድንበር ተሻጋሪ የውኃ ሀብት ተጠቃሚነትን በተግባር ማስመስከሯን አስረድተዋል። ግብፅ ለዓባይ ወንዝ የውኃ ምንጭ ምንም ዓይነት አበርክቶ የላትም ያሉት ተመራማሪው፤ ለሺህ ዘመናት ለብቻየ ልጠቀም የሚለው እሳቤም ኢ-ፍትሐዊ ከመሆኑም ባሻገር መሠረተ ቢስ ፍላጎት ነው ብለዋል። የተፋሰሱን ሀገራት የዓባይ ወንዝ የጋራ ተጠቃሚነት ድርድርና ስምምነቶች በማስተጓጎልም የተሳሳተ አማራጭን እየተከተለች እንደሚገኝ ተናግረዋል። ኢትዮጵያም እስካሁን የውኃ ሀብቶቿን የታችኞቹን የተፋሰስ ሀገራትና ጎረቤቶቿን በማይጎዳ መንገድ ማልማቷን አጠናክራ መቀጠል እንዳለባት አስገንዝበዋል። ግብፅ በሕዳሴ ግድብና በዓባይ ወንዝ ላይ የምታስተጋባው የተሳሳተ መረጃም መሠረተ ቢስ ክስና ማረጋገጫ የሌለው የሺህ ዘመናት ስሁት ትርክት ውጤት መሆኑን አብራርተዋል። ሕዳሴ ግድብና ሌሎች የኃይል ማመንጫ ግድቦች የኢትዮጵያን የውኃ ልማት ዕውቀት፣ ልምድና ተሞክሮ ወደ ላቀ ደረጃ አሸጋግሯል ብለዋል። በቀጣይም በዓለም አቀፍ ሕግና መርህ በመመስረት በዓባይና ሌሎች የውኃ ሀብቶች ላይ ሁለንተናዊ ዕድገትና ብልፅግናን የሚያረጋግጥ የልማት ሥራን ማስቀጠል እንዳለባት ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ለውጭ ሀገራት ከቀረበው የኃይል ሽያጭ 475 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝታለች-ኢንጂነር አሸብር ባልቻ
Aug 28, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22 /2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ለውጭ ሀገራት ከቀረበው የኃይል ሽያጭ 475 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ አስታወቁ። ኢንጂነር አሸብር ባልቻ፤ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2019 የትኩረት አቅጣጫዎችን በማስመልከት ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም፤ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ካለፈው በጀት ዓመት በ23 በመቶ ዕድገት በማስመዝገብ የማመንጨት አቅሙ 9 ሺህ 730 ሜጋ ዋት መድረሱን አስታውቀዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ የ124 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ገቢ በማስገኘት የ39 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማስመዝገብ እንደቻለ አስታውቀዋል። የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት የተሳካው አጠቃላይ የእቅዱ 101 ነጥብ 83 ከመቶ አፈጻጸም በተቋሙ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተመዘገበ የትርፍ አፈጻጸም ስኬት መሆኑን አብራርተዋል። ለውጭ ሀገራት ከቀረበው የኃይል ሽያጭም 475 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን ገልጸው፤ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸርም የ25 በመቶ ብልጫ አለው ብለዋል። በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ ከተመረተው የኤሌክትሪክ ኃይልም የውኃ ማመንጫዎች 97 በመቶ ድርሻ መያዙን ገልጸዋል። በቀጣይም የገናሌ ዳዋ 6 የውኃ ኃይል ማመንጫ፣ የአይሻ 2ኛ የንፋስ ኃይል ማመንጫና በሀገር ውስጥ ፋይናንስ የሚገነባ የ100 ሜጋ ዋት የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶችን ለማስጀመር እቅድ መያዙን አስታውቀዋል። በተጨማሪም የአይሻ ንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ 40 ሜጋ ዋት ኃይል ያመነጫል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል።
በኦሮሚያ ክልል የቱሪስት ፍሰትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት የዘርፉ ገቢ እንዲጨምር አስችሏል
Aug 28, 2026 96
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የቱሪስቶችን ፍሰት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት የዘርፉን የገቢ ምንጭነት እያሳደጉት መምጣታቸውን የክልሉ ደንና የዱር እንስሳት ቢሮ አስታወቀ። የኦሮሚያ ደንና የዱር እንስሳት ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አራርሳ ረጋሳ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የደን ሃብትን በማልማት ለአካባቢ ጥበቃ ትልቅ ትኩረት ከመስጠት ባሻገር የቱሪዝም መስህብና የሀብት ምንጭ ማድረግ ስለመቻሉ አንስተዋል። በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ የደን ሽፋን በማደጉ የዱር እንስሳት ደህንነት እንዲጠበቅና ሸሽተው የነበሩም እንዲመለሱና ይበልጥ እንዲበራከቱ እድል ተፈጥሯል ብለዋል። በዚህም የዱር እንስሳትና ብርቅዬ አእዋፋት ጭምር ሁነኛ የጎብኝዎች መስህብ እየሆኑ በመምጣታቸው አበረታች ገቢ እየተገኘ መሆኑን ገልጸዋል። የዘርፉ ልማት የስነ-ምህዳር መታደስን ከመፍጠሩ በላይ፣ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶችን ትኩረት መሳብ ያስቻለ ስለመሆኑም አስረድተዋል። በክልሉ የሚገኙ ብሔራዊ ፓርኮችን ተፈጥሮአዊ ሀብት ከመጠበቅ ጎን ለጎን ሕጋዊ የአደን ስፍራዎችን በመለየት የገቢ ምንጭ እንዲሆኑ ማድረግ ተችሏል ነው ያሉት። በእርጅና ላይ የሚገኙና ጉዳት የደረሰባቸውን የዱር እንስሳት በመለየትም እንክብካቤ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከቻይናዋ ቼንዱ ከተማ አዲስ የካርጎ በረራ አስጀምሯል
Aug 28, 2026 111
አዲስ አበባ፣ነሐሴ 22/ 2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከቻይናዋ ቼንዱ ከተማ አዲስ የካርጎ በረራ በዛሬው ዕለት ማስጀመሩን አስታወቀ። የተጀመረው የካርጎ በረራ በደቡብ ምዕራብ ቻይና እና አፍሪካ መካከል አዲስ የካርጎ ትራንስፖርት መስመር የከፈተ መሆኑን አስታውቋል፡፡ አገልግሎቱ በምዕራብ ቻይና እና በአፍሪካ መካከል ያለውን የንግድ እና የኢኮኖሚ ትስስር የሚያጠናክርና የሚደግፍ መሆኑን የኢትዮጵያ የአየር መንገዱ አመልክቷል፡፡
ግብፅ ለኢትዮጵያ ተገቢውን ዋጋ መክፈል አለባት-አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ
Aug 27, 2026 738
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ለምታበረክተው የ86 በመቶ የውሃ ሀብት ድርሻ ግብፅ ተገቢውን ዋጋ መክፈል እንዳለባት የቀድሞ የውሃ ሀብት ሚኒስትር አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ ገለጹ። ኢትዮጵያ በዓባይና በሌሎች ታላላቅ ወንዞቿ ላይ የመስኖ ግድብ በመገንባት ሁለንተናዊ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል የግብርና ምርታማነትን ማፋጠን እንዳለባትም አምባሳደር ሽፈራው አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሀብቶቿ የዘመናት ዕዳዎቿ እስኪመስሏት ድረስ ግብፅ በሸረበችው ሴራ አማካኝነት ሳትጠቀም ብትቆይም፤ ኢትዮጵያዊያን የተሸረበባቸውን ሴራ በመበጠስ በዓባይ ወንዝ ላይ ታላቁን የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በመገንባት ብርሃን በመፈንጠቅ አንድነታቸውን አሳይተዋል። በአሁኑ ወቅት ከታላቁ ሕዳሴ ግድብ በሚመነጨው የኤሌክትሪክ ኃይል ከሀገር በመሻገር ቀጣናዊ የኢኮኖሚ በረከት ለመፍጠር ተችሏል። በታላቁ ሕዳሴ ግድብ የተፈጠረው ቀጣናዊ የኃይል ትስስርም የኢትዮጵያን በጋራ የማደግ አፍሪካዊ ርዕይን በአደባባይ የገለጠ አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደት ትልም ሆኖ ተመዝግቧል። የኢትዮጵያ የቀድሞ የውሃ ሀብት ሚኒስትር አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ ግብፅ ለረጅም ዘመናት በምትከተለው ዓባይን የመቆጣጠር ፖሊሲ ምክንያት ኢትዮጵያ ዓባይን ሳትጠቀም ቆይታለች። ለረጅም ዘመናት ግብፅ በኢትዮጵያ ላይ የጠላትነት ትርክት ስታራምድ መቆየቷን ጠቁመው፤ በዚህም ኢትዮጵያ የዓባይን ውሃ በማልማት ሳትጠቀም ዓመታትን ማሳለፏን ተናግረዋል። በዚህ ቁጭት ኢትዮጵያውያን በሕብረ ብሔራዊ አንድነት በፓን አፍሪካኒዝም መንፈስ ግዙፉን ዓለም አቀፍ የኃይል ማመንጫ ታላቁ ሕዳሴ ግድብን እውን ማድረጋቸውን ገልጸዋል። ታላቁ ሕዳሴ ግድብ የኢትዮጵያውያንን የመፈጸም አቅም በዓለም መድረክ ያሳየ ታሪካዊ የትውልድ አሻራ መሆኑን አውስተው፤ ለታችኛው ተፋሰስ ሀገራት አስተማማኝ የውሃ ፍሰት እንዲያገኙ በማድረግ የጎርፍ አደጋንና የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቀነስ ትልቅ ጥቅም እያስገኘ መሆኑን አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ከጅቡቲ፣ ኬንያ፣ ሱዳንና ሌሎች የቀጣናው ሀገራት ጋር የፈጠረችው የኃይል ትስስርም ቀጣናዊና አህጉራዊ ኢኮኖሚያዊ ውህደትን ለማፋጠን ጉልህ ፋይዳ እያበረከተም መሆኑን ገልጸዋል። በታላቁ ሕዳሴ ግድብ ላይ የተፈጠረው ቀጣናዊ የኃይል ትስስርም ኢትዮጵያ ከደቡብ አፍሪካ ጫፍ እስከ አውሮፓ አባል ሀገራት የሚሻገር የኃይል ትስስር የማጠናከር አቅም እንዳላት ማሳያ ነው ብለዋል። የኃይል አቅርቦት አስተማማኝነት የአንድን ሀገር ልማትና ዕድገት ከማሳለጥ ባሻገር በትብብር የማደግ ርዕይን የሚያሳካ ወሳኝ መሠረተ ልማት መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያን በታሪካዊ ጠላትነት የምትመለከትበት የግብፅ የትርክት ሴራ በአንድ በኩል የውሃ ጉዳይን ከፖለቲካ ጋር እንዲቆራኝ ሲያደርግ በሌላ በኩል ደግሞ በአካባቢው የትብብር ሂደት ላይ ተጽዕኖ እያሳደረ ነው ብለዋል። በትብብር መንፈስ መሥራት ከተቻለ ኢትዮጵያ በግድቦቿ የምታከማቸውን የውሃ መጠን በመቆጣጠር የጎርፍ ተጋላጭነትን ከመቀነስ ባሻገር በድርቅ ወቅት የሚጠቅም የውሃ አስተዳደር ሥርዓት ማስፋፋት እንደሚቻል ነው ያመለከቱት። ሀገራት በፍትሐዊና ምክንያታዊ ተጠቃሚነት መርህ ላይ ተመሥርተው አብረው ማደግ አለባቸው ያሉት አምባሳደሩ፤ ለዚህም ግብፅ ከግጭትና ከጠላትነት ትርክት በመውጣት የትብብር መንፈስን መከተል እንዳለባት አስገንዝበዋል። ግብፅ በዓባይ ወንዝ ላይ ከምታራምደው የብቻ የተጠቃሚነት ፍላጎትና አቀራረብ በመላቀቅ የዓባይ ተፋሰስ ሀገራት የውሃ ሀብታቸውን በፍትሐዊና ምክንያታዊ መንገድ እንዲጠቀሙ በትብብር መሥራት እንዳለባት ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ለምታበረክተው የ86 በመቶ የውሃ ሀብት ድርሻ ግብፅ ተገቢውን ዋጋ መክፈል እንደሚጠበቅባትም ነው የተናገሩት። በቀጣይም ኢትዮጵያ ዓባይ ወንዝን ጨምሮ በሌሎች ድንበር ተሻጋሪ ወንዞቿ ላይ ተጨማሪ ግድቦችን በመገንባት የኃይልና የመስኖ አቅሟን ማሳደግ እንዳለባት አምባሳደር ሽፈራው አስገንዝበዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያ ተጨማሪ የኃይል ማመንጫ ግድቦችንና የመስኖ ፕሮጀክቶችን ለመገንባት የሚያስችላትን የሰው ኃይል፣ የገንዘብ አቅም፣ ልምድና ተሞክሮ ለማዳበር አስተዋጽኦ ማድረጉንም ጠቁመዋል። በዚህም የግብርና ምርታማነትን የበለጠ ለማሻሻል በዓባይና በሌሎች የውሃ ሀብት ወንዞቿ ላይ የመስኖ ልማትን በስፋት በማከናወን የምግብ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጡ ግድቦችን መገንባት እንደሚኖርባት አብራርተዋል። በዓባይ ተፋሰስ ሀገራት መካከል የውሃ ሀብትን በፍትሐዊና ምክንያታዊ መንገድ መጠቀም፣ መጠበቅና በትብብር ማልማትን ያለመው የናይል ወንዝ ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት በተፋሰሱ ሀገራት መካከል የጋራ የውሃ አስተዳደር ሥርዓትን ለማጠናከር ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። የናይል ትብብር ማዕቀፉን ኢትዮጵያ፣ ሩዋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ ዑጋንዳ፣ ቡሩንዲ፣ ኬንያና ደቡብ ሱዳን የፈረሙት ሲሆን፤ የቅኝ ግዛት ዘመን ስምምነቶችን ደጋግመው የሚያነሱት ግብፅና ሱዳን ግን ማዕቀፉን እስካሁን አልፈረሙትም። አምባሳደር ሽፈራው እንደሚሉት፤ ግብፅና ሱዳን የናይል የትብብር ማዕቀፉን አለመፈረማቸው በቅኝ ግዛት ዘመን በብቸኝነት የመጠቀም ኢ-ፍትሐዊ አካሄድን ለማስቀጠል ከሚመነጭ ለብቻ የመጠቀም ፍላጎት ነው። በአሁኑ ወቅትም ግብፅ የናይል የጋራ ትብብር ማዕቀፍ ተዘጋጅቶ እያለ በራሷ መንገድ ትብብር ለመፍጠር ጥረት የምታደርገው ፍትሐዊ የውሃ ሀብት የጋራ ተጠቃሚነትን የማትቀበል መሆኗን በገሃድ የሚገልጥ የአደባባይ ሐቅ ነው ብለዋል።
በሲዳማ ክልል ከተሞችን ይበልጥ በማዘመን ለስራና ለኑሮ ምቹ የማድረግ ጥረት በተቀናጀ መልኩ እየተሰራ ነው -ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Aug 27, 2026 123
ሀዋሳ፤ ነሀሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል ከተሞችን ይበልጥ በማዘመን ለስራና ለኑሮ ምቹ የማድረግ ጥረት በተቀናጀ መልኩ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። የክልል፣ የዞንና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች በሀዋሳ፣ ይርጋለም፣ አለታ ጩኮና አለታ ወንዶ ከተሞች እየተሰሩ ያሉ የኮሪደር፣ የሀይቅ ዳርቻ ልማት፣ የመሶብ አንድ ማእከል አገልግሎት፣የትምህርትና ሌሎችም መሰረተ ልማቶችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ፤ በክልሉ እየተከናወኑ ያሉ ሁለንተናዊ የልማት ስራዎች የላቀ ስኬት እየተመዘገበባቸው ይገኛል ብለዋል። ከጉብኝቱ በኋላ ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት በክልሉ የሚገኙ ከተሞችን ለስራ፣ ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ እና መልካም አስተዳደር የሰፈነባቸው እንዲሆኑ ለማድረግ የተለያዩ የልማት ስራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ይገኛል። የሀዋሳ ኮሪደር ልማት አራተኛውን ዙር ለአገልግሎት ማብቃት እንደተቻለ የተናገሩት ርዕሰ መስተዳድሩ በይርጋለም፣ አለታ ወንዶ፣ ወንዶገነት፣ ዳዬና ለኩ ከተሞችም በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በሀዋሳ ከኮሪደር ልማቱ ጎን ለጎን የሀይቅ ዳርቻ ልማት ስራ በጥራትና በፍጥነት እየተከናወነ መሆኑን አንስተው በተያዘለት ጊዜ ገደብ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ ሌት ከቀን ያለምንም እረፍት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በሲዳማ ክልል ሀዋሳን ጨምሮ ሌሎች ከተሞችንም ይበልጥ በማዘመን ለስራና ለኑሮ ምቹ የማድረግ ጥረት በተቀናጀ መልኩ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ ስድስት ከተሞች የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ማዕከላት ግንባታ በጥሩ ሁኔታ እየተከናወነ መሆኑን አንስተው የሲዳማና የሀዋሳ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎቶች ወደ ስራ በመግባት ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን አንስተዋል። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደርና የሀይቅ ዳርቻ ልማት ስራዎች ሀዋሳን በአፍሪካ ተመራጭ የቱሪዝምና የኮንፈረንስ ማዕከል ለማድረግ የሚያስችል መሰረት የተጣለባቸው ናቸው ብለዋል። አራተኛው ዙር የኮሪደር ልማት ስራ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉን ጠቁመው የሀይቅ ዳርቻ ልማቱንም በታቀደለት ጊዜ በጥራት ሰርቶ ለማጠናቀቅ ሰባቱንም ቀን ለ24 ሰዓት እየተሰራ እንደሚገኝም አስረድተዋል። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ በየነ በራሳ በበኩላቸው በክልሉ የትምህርት ስብራትን በመጠገን የተሟላ ዕውቀትና ስብዕና የተላበሰ ዜጋን ለማፍራት በሚያስችል መልኩ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም በፌዴራል፣ በክልሉ መንግስት፣ በማህበረሰቡና አጋዥ ድርጅቶች የትምህርት ቤቶችን ደረጃ የማሻሻልና የአዳዲስ ትምህርት ቤቶች ግንባታ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። እየተገነቡ ከሚገኙ ትምህርት ቤቶች ውስጥ በትምህርት ሚኒስቴር እየተገነባ ያለውና በአለታ ጩኮ ከተማ የሚገኘው የሩፎ ዋኢኖ ሞዴል ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በ2019 የትምህርት ዘመን ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር ዝግጁ መደረጉን ገልጸዋል። የደቡባዊ ሲዳማ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መንገሻ ፊታሞ እንዳሉት በዞኑ የኮሪደር ልማትን ተደራሽ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት ተገኝቷል። በዞኑ አለታ ወንዶን ጨምሮ በሶስት ከተሞች የተለያዩ አገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ያካተተ የኮሪደር ልማት እየተካሄደ እንደሚገኝና የአለታ ወንዶ ከተማን በቅርቡ ለአገልግሎት ክፍት ለማድረግ ርብርብ እየተደረገ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ በጉብኝቱ ላይ በብልጽግና ፓርቲ የሲዳማ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አብርሃም ማርሻሎን ጨምሮ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የዞኖች፣ የወረዳና የከተሞቹ አመራሮች ተገኝተዋል።
በከተማው ተግባራዊ የተደረገው የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም ለልማትና መልካም አስተዳደር ስኬቶች አዎንታዊ አስተዋጽኦ አበርክቷል
Aug 27, 2026 113
ደብረ ብርሃን፤ ነሀሴ 21/2018 (ኢዜአ)፡- በደብረ ብርሃን ከተማ ተግባራዊ የተደረገው የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም ለልማትና መልካም አስተዳደር ስኬቶች አዎንታዊ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የከተማ አስተዳደሩ ገለጸ። የከተማ አስተዳደሩ ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት መምሪያ የ2018 በጀት ዓመት የተቋማት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ትውውቅ የውይይት መድረክ አካሄዷል። በመድረኩ ላይ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብእሸት እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ሰላምን ከማስፈን ጎን ለጎን በልማትና በመልካም አስተዳደር ሥራዎች አመርቂ ውጤት ተመዝግቧል። በተለይም በሰላም ማስፈን፣ በመሠረተ ልማት ግንባታ፣ ኢንቨስትመንትን መሳብና በሌሎች የልማት ሥራዎች አበረታች ውጤት እንዲመጣ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርሙ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። አክለውም የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ ለማስቀጠል ሲቪል ሰርቪሱን ከብልሹ አሠራርና ከሙስና የጸዳ ማድረግ እንደሚገባም አስረድተዋል። የከተማ አስተዳደሩ ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ እስክንድር ገብረሚካኤል በበኩላቸው፤ የተተገበሩ አዳዲስ የሪፎርም ሥራዎች የሠራተኛውን ተነሳሽነት እንዳሳደጉ ተናግረዋል። የአገልግሎት አሰጣጥ ተግዳሮቶችን ለመፍታት የተደረገው ጥረት በከተማዋ ዘርፈ ብዙ የልማት ውጤቶች እንዲመዘገቡ ማድረጉን አብራርተዋል። የውይይቱ ተሳታፊ ወይዘሮ መሠረት ምትክ በበኩላቸው፤ በሥራ ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን በመቅረፍና አሠራርን በማሻሻል ሕብረተሰቡን በላቀ ደረጃ ለማገልገል መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። አክለውም የተገልጋዩን እርካታ ለማሳደግ መሰል የመድረክ ውይይቶች አስፈላጊ መሆናቸውንም ጠቁመዋል። አሠራሮችን በማሻሻል ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት የተደረገው ጥረት ለሠራተኛው ተጨማሪ ተነሳሽነትን እንደፈጠረ የገለፁት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ አሳምነው ወልደተንሳይ ናቸው።
በክልሉ ግብርናን በማዘመን የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ሆነዋል
Aug 27, 2026 109
ጊዶሌ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርናን በማዘመን የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸው ተገለጸ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ከ64 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በጋርዱላ ዞን ያስገነባው የአርጎባ አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክት ተመርቋል። በምረቃ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አማካሪ ቦሼ ቦምቤ (ዶ/ር) እንደገለጹት በክልሉ በመደመር መንግሥት እሳቤ የተከናወኑ የልማት ተግባራት የህዝብን ተጠቃሚነት እያሳደጉ ነው። በተለይ የመስኖ አውታር መስፋፋቱ ወቅትን ጠብቆ ብቻ ግብርናን የማከናወን ባህልን ከመቀየር ባለፈ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥና ገቢን ለማሳደግ ማገዙን ጠቁመዋል። የክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር በበኩላቸው እንዳሉት፤ በክልሉ የከርሰ ምድርና ገጸ ምድር ውሃ ሀብቶችን በመጠቀም አነስተኛና መካከለኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች ለማሳካት እየተሰራ ነው። በዚህም በተቀናጀ የውሃ ሀብት አስተዳደር የመስኖ ልማትን በማስፋፋት የአርሶና አርብቶ አደሮችን የምግብ ዋስትናና ገቢ ለማሻሻል ትኩረት መሰጠቱን ነው የገለጹት። በጋርዱላ ዞን የተገነባው የአርጎባ አነስተኛ መስኖ ፕሮጀክት የዚሁ አካል መሆኑን ጠቁመው፤ ፕሮጀክቱ 180 ሄክታር መሬት በማልማት ከ800 በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል። የጋርዱላ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ግንኙነት ኪታሞ የመስኖ ፕሮጀክቱ የህዝቡን የልማት ጥያቄ ምላሽ የሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። ፕሮጀክቱ ዘላቂ ጠቀሜታ እንዲኖረውም ማህበረሰቡ አስፈላጊውን ጥበቃና እንክብካቤ እንዲያደርግ ይሠራል ብለዋል። በዞኑ የአርጎባ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ንጉሤ ዳትኮ እና ካምባታ ካሊላ እንዳሉት፣ በአካባቢያቸው የተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት የዝናብ ወቅት ብቻ ጠብቀው ከማልማት እንዳሻገራቸው ተናግረዋል። የመስኖ መሰረተ ልማቱን በሀላፊነት በመጠበቅ በዓመት ሦስት ጊዜ በማምረት ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ጠንክረው እየሰሩ መሆናቸውንም አክለዋል።
ግብርን በታማኝነትና በወቅቱ በመክፈል ልማትን ለማፋጠን የዜግነት ግዴታችንን እየተወጣን ነው- በድሬዳዋ ተሸላሚ ግብር ከፋዮች
Aug 27, 2026 83
ድሬዳዋ፣ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፡-ግብርን በታማኝነትና በወቅቱ በመክፈል ልማትን ለማፋጠን የዜግነት ግዴታቸውን እየተወጡ መሆናቸውን በድሬዳዋ ዕውቅናና ሽልማት የተሰጣቸው ግብር ከፋዮች ገለጹ። የድሬዳዋ አስተዳደር በ2016 እና በ2017 ዓ.ም ግብራቸውን በታማኝነት ለከፈሉ የንግዱ ማህበረሰብ አባላት ዕውቅናና ሽልማት ሰጥቷል። ሽልማትና ዕውቅና የተሰጣቸው ግብር ከፋዮች ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የመንግስት ግብርን በታማኝነትና በወቅቱ በመክፈል ለድሬዳዋ ሁለንተናዊ ዕድገት የድርሻቸውን እየተወጡ ናቸው፡፡ አስተዳደሩም ለታማኝ ግብር ከፋዮች በየዓመቱ ዕውቅናና ሽልማት መስጠቱ ግብር ከፋዩ የዜግነት ሀላፊነቱን በታማኝነትና በወቅቱ እንዲወጣ ተነሳሽነት እየፈጠረ መሆኑን ገልፀዋል። ከተሸላማዊቹ መካከል በሆቴል ሥራ የተሰማሩት ኤፍራታ ሚካኤል ግብራቸውን በወቅቱና በታማኝነት በመክፈላቸው የተሰጣቸው ዕውቅና እና ሽልማት ለሌሎች ምሳሌ የሚሆን ነው። የከፈሉት ግብር ለድሬዳዋም ሆነ ለሀገር እድገት ጠቀሜታ ስላለው የዜግነት ግዴታቸውን መወጣታቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቁመዋል። ግብርን በታማኝነት ከፍሎ የዜግነት ግዴታን መወጣት ለአዕምሮ ሰላም የሚሰጥና ስራን በራስ መተማመን ለመፈፀም ያስችላል ያሉት ደግሞ ሌላው ተሸላሚ አቶ አስቻለው ብሩ ናቸው። የንግዱ ማህበረሰብ ግብሩን በወቅቱና በታማኝነት መክፈሉ የድሬዳዋን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ልማቶች ለማፋጠን ስለሚያግዝ ተግባሩን ማጠናከር እንዳለበት አስረድተዋል። ሌላው ተሸላሚ አቶ አሪፍ ጣሂር በበኩላቸው አስተዳደሩ የሰጣቸው የምስጉን ግብር ከፋይ ዕውቅናና ሽልማት የዜግነት ኃላፊነታቸውን ይበልጥ ለመወጣት እንዳነሳሳቸው አስታውቀዋል። አስተዳደሩ ግብርን በቴክኖሎጂ መክፈል የሚያስችል አሰራር መዘርጋቱ የግብር ከፋዩን እንግልት ከማስቀረት ባለፈ ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኝ በማስቻሉ መቀጠል አለበት ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በድሬዳዋ ለተመዘገቡ አበረታች የልማት ውጤቶች የታማኝ ግብር ከፋዮች ድርሻ የጎላ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ናቸው። በአስተዳደሩ የግብር አሰባሰቡን ለማዘመንና ለማቀላጠፍ ዲጂታል አሰራርን ተደራሽ የማድረግ ሥራ መከናወኑንም አስታውቀዋል። አስተዳደሩ ታማኝ ግብር ከፋዮችን ከማበረታታት ባለፈ በህገ ወጦች ላይ ተገቢውን እርምጃ የመወሰዱ ሥራውን አጠናክሮ መቀጠሉንም አስታውቀዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር እና ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች ለታማኝ ግብር ከፋዮች የተዘጋጁ ሽልማቶችን አበርክተዋል።
በአማራ ክልል የጥጥ ምርትን በጥራትና በብዛት በማምረት ለጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪዎች ለማቅረብ ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል
Aug 27, 2026 80
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 21/2018(ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የጥጥ ልማትን በጥራትና በብዛት በማምረት ለጨርቃ ጨርቅ ኢንዱስትሪዎች በግብአትነት ለማቅረብ ልዩ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የጥጥ ልማት አስተባባሪ አቶ ኤልያስ በላይ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ የሚካሄደው የጥጥ ልማት ከውጭ የሚገባን የጥጥ ምርት በሀገር ውስጥ ለመተካት የሚያስችል ነው። በዚህም በተያዘው የክረምት ወቅት በክልሉ ቆላማ አካባቢዎች 75 ሺህ 717 ሄክታር መሬት በጥጥ መልማቱንና ከዚህም አንድ ሚሊዮን 945 ሺህ ኩንታል የሚጠጋ ምርት እንደሚጠበቅ ገልጸዋል። በዚህም የጥጥ ምርትን በጥራትና በብዛት በማምረት ለጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪዎች በግብአትነት ለማቅረብ ግብ ተይዞ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። ከዘር እስከ ምርት አሰባሰብ ባለው ሂደት ጥራቱን ጠብቆ ጥጥ ለማምረት እየተደረገ ያለውን ጥረት በግብርና ሚኒስቴር ስር የተቋቋመው የጥጥ ልማት ባለስልጣን ክትትልና ድጋፍ እያደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። ለአልሚ ባለሃብቶችና አርሶ አደሮች የአቅም ግንባታ ስልጠናዎችን በመስጠት የጥጥ ልማት ሥራው በሜካናይዜሽን ታግዞ እንዲከናወን መደረጉንም አመልክተዋል። በጥጥ ልማት ሥራ ከተሰማሩት መካከል በምዕራብ ጎንደር ዞን የምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ አርሶ አደር ዘውዱ ፈቃዴ አምስት ሄክታር መሬታቸውን በጥጥ በማልማት እየተንከባከቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። ምርታማነታቸውን ለማሳደግና ጥራቱን ለማስጠበቅ የተሰጣቸው ስልጠና ጥራት ያለው ጥጥ በማምረት ለኢንዱስትሪዎች ለማቅረብ እንደሚያግዛቸው አስረድተዋል። መንግስት ለጥጥ ልማት ትኩረት መስጠቱ ሁለት ሄክታር ተኩል ማሳቸውን በጥጥ ለማልማት እንዳነሳሳቸው የገለጹት ደግሞ የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር መከተ ገብሬ ናቸው። በክልሉ ባለፈው የምርት ዘመን በጥጥ ከለማው 58 ሺህ 527 ሄክታር መሬት 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ምርት ለኢንዱስትሪዎች መቅረቡን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያሳያል።