ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በሶማሌ ክልል የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች በተቀናጀ መልኩ እየተከናወኑ ነው - ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ
Aug 29, 2026 97
ጅግጅጋ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል የተቋማትና የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች በተቀናጀ መልኩ እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ፤ የክልሉን ኢንቨስትመንትና የኢንዱስትሪና ቢሮ አዲስና ዘመናዊ የህንፃ ግንባታ አስጀምረዋል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ባደረጉት ንግግርም በክልሉ የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሁለንተናዊ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። ከልማት ስራዎች በተጓዳኝ የመንግስት አገልግሎቶችን ምቹ፣ ፈጣንና ቀልጣፋ የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን አንስተዋል። በዛሬው እለትም የክልሉን ኢንቨስትመንትና የኢንዱስትሪና ቢሮ አዲስና ዘመናዊ የህንፃ ግንባታ መጀመሩን ገልጸው፤ የተቋማትና የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች ይቀጥላሉ ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን የትምህርት፣ የውሃ፣ የመንገድ፣ የጤና የዲጂታል ልማትና ሌሎችም ስራዎች በልዩ ትኩረት እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። በክልሉ ከተሞችም ይሁን በገጠር ሰው ተኮር የሆኑ ልማቶችን የመገንባትና የዜጎችን ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራ ዋነኛ ትኩረታችን ሆኖ ይቀጥላል ብለዋል።
በሐረሪ ክልል እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች የሐረር ከተማን የቱሪዝም መዳረሻነት እያሳደጉ ነው
Aug 29, 2026 79
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ) ፦ በሐረሪ ክልል እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች የሐረር ከተማን የቱሪዝም መዳረሻነት በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞችን እያስገኙ መሆናቸውን የክልሉ ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሚ አብዱልዋሲ ገለጹ። መንግሥት ካለፉት ዓመታት ወዲህ በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ የቱሪዝም ሀብቶችን በመግለጥ፣ በርካታ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎችን በማልማትና ለነባሮቹም እሴት የሚጨምሩ ተግባራትን በማከናወን የኢትዮጵያን የቱሪዝም መዳረሻነት እያሳደገ ይገኛል። የክልሉ ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሚ አብዱልዋሲ እንደገለጹት፤ የክልሉን እምቅ የቱሪዝም ሃብት አልምቶ በመጠቀም ከፍተኛ ለውጥ እየተመዘገበ ነው። በተለይም በመደመር መንግስት ቱሪዝም ከዋና የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ አንዱ ሆኖ መወሰዱና ትኩረት መሰጠቱ ዘላቂነት ያለው እድገት እንዲመዘገብ ማስቻሉን ገልፀዋል። በዚህም ባለፉት ጥቂት ዓመታት በክልሉ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎችን ከማልማት ባሻገር ነባር ቅርሶችን በመጠገንና በመንከባከብ ሰፋፊ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል ብለዋል። በጁገል አለም አቀፍ ቅርስ እድሳትን ጨምሮ ነባርና አዳዲስ የቱሪዝም መዳረሻ ልማት ስራዎችና መሰል ተግባራት የክልሉ ቱሪዝም በፍጥነት እንዲነቃቃ እያደረገ መሆኑንም በማሳያነት ጠቅሰዋል። በተጨማሪም በዘርፉ በተከናወኑ ተግባራት የሃገር ውስጥም ሆነ የውጭ ሃገራት ጎብኚዎች ቁጥር እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በክልሉ የቱሪስት መስህብ ሃብቶችን የማስተዋወቅ፣ መዳረሻ ስፍራዎችን የማልማትና መሰረተ ልማቶችን የማሟላት ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስገንዝበዋል።
በክልሉ የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናክረው ቀጥለዋል- ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Aug 29, 2026 106
ጉንችሬ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሕብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። በጉራጌ ዞን ጉንችሬ ከተማ አስተዳደር የተገነቡት የጉንችሬ ጤና ጣቢያ እና የጉንችሬ ብራይት አንደኛ እና ቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተመርቀው ለአገልግሎት በቅተዋል። ፕሮጀክቶቹን የመረቁት ርዕሰ መስተዳደር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ይገኛሉ። ለአብነትም ዛሬ ከተመረቁት የጤናና የትምህርት ተቋማት በተጨማሪ የገበያ ማዕከላት እና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ግንባታ መከናወኑን ጠቅሰዋል። ፕሮጀክቶቹ ለማህበረሰቡ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ የክልሉ መንግስት የህዝብን ፍላጎት ለማሟላት ከምንጊዜውም በላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ዛሬ የተመረቁት ፕሮጀክቶች መንግስት የማህበረሰቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የጀመረውን ተግባር እውን ለማድረግ ያለውን ቁርጠኝነት ያሳያሉ ሲሉም አክለዋል። ጥራት ያለው የጤና አገልግሎት ተደራሽ ለማድረግ እና በእውቀት የታነጹ ምስጉን ተማሪዎችን ለማፍራት በሚደረገው ጥረት ፕሮጀክቶቹ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖራቸውም አመልክተዋል። በክልሉ የሕብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል ርስቱ ይርዳው የጉንችሬ እና በዙሪያው ያሉ ነዋሪዎች በጤናና በትምህርት ተቋማት እጥረት የተነሳ ሲቸገሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። መንግስት ህብረተሰቡንና ረጂ ድርጅቶችን በማስተባበር ያስገነባቸውና ዛሬ ለምረቃ የበቁት ፕሮጀክቶች ይህን ችግር እንደሚፈቱ ጠቅሰው፣ ማህበረሰቡ ፕሮጀክቶቹን ከመጠበቅ ባለፈ ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ የበኩሉን እንዲወጣ አሳስበዋል። የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ የጤና ተቋሙ እና የትምህርት ቤቶቹ ግንባታ በዞኑ ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ገንብቶ የመጨረስ ማሳያ ናቸው ብለዋል። ፕሮጀክቶቹ የማህበራዊ አገልግሎት ተቋማትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ የልማት ጥያቄን ምላሽ ለመስጠት ማስቻላቸውንም ተናግረዋል። የጉንችሬ ከተማ ከንቲባ አቶ አብድልቋድር ሂጅራ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የማህበረሰቡን ጤና ለማሻሻል እና ጥራት ያለው ትምህርት ተደራሽ ለማድረግ የፕሮጀክቶቹ መገንባት ትልቅ አስተዋጽኦ አለው። በፕሮጀክቶቹ የምረቃ መርሀ ግብሩ ላይ የፌደራል፣ የክልል፣ የጉራጌ ዞን እና የጉንችሬ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮችና ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ ከታይላንድ ጋር ያላትን ዘመናት ያስቆጠረ ወዳጅነት ወደ ላቀ የኢኮኖሚ፣ የንግድና የኢንቨስትመንት አጋርነት ለመቀየር ቁርጠኛ ናት- አምባሳደር ደዋኖ ከድር
Aug 29, 2026 109
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከታይላንድ ጋር ያላትን ዘመናት ያስቆጠረ ወዳጅነት ወደ ላቀ የኢኮኖሚ፣ የንግድና የኢንቨስትመንት አጋርነት ለመቀየር ቁርጠኛ መሆኗን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምስራቅ፣ እስያና ፓስፊክ ሀገራት ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር ደዋኖ ከድር ገለጹ። በኢትዮጵያ የታይላንድ ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ጂሩሳያ ቢራናንዳ በበኩላቸው ታይላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የንግድና የኢኮኖሚ ትብብሯን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ፍላጎት እንዳላት ተናግረዋል። "ታይላንድ-ኢትዮጵያ፡ የቢዝነስ ግንኙነትን መገንባት" በሚል መሪ ሃሳብ የታይላንድ-ኢትዮጵያ የቢዝነስ ፎረም እየተካሄደ ነው። በፎረሙ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎችን ጨምሮ የኢትዮጵያ እና የታይላንድ የንግድ ማህበረሰብ አባላት እየተሳተፉ ይገኛሉ። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምስራቅ፣ እስያና ፓስፊክ ሀገራት ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር ደዋኖ ከድር በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ረጅም ታሪክ ያለው ነው። ይህንን የፖለቲካ ግንኙነቱን ወደ ተጨባጭ የንግድና የኢኮኖሚ ትስስር ማሸጋገር እንደሚገባ ተናግረዋል። በተለይም ታይላንድ በቱሪዝም፣ በግብርና ማቀነባበሪያ፣ በፋርማሲዩቲካልስ እና በቴክኖሎጂ ዘርፎች ያላትን የበለጸገ ልምድ ወደ ኢትዮጵያ ማምጣት እንደሚቻል ገልጸዋል። በተጨማሪም ታይላንድ አዲስ ይፋ ያደረገችውን "የአፍሪካ-ታይላንድ ኢኒሼቲቭ" አድንቀው፤ ጥረቱን ወደ ተጨባጭ የድርጊት መርሃ ግብር በመቀየር ግንኙነቱን የበለጠ ለማጠናከር እንደሚሰራ አስታውቀዋል። ኢትዮጵያ በግብርና፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም፣ በኢንዱስትሪ እና በቴክኖሎጂ ዘርፎች ሰፊ የኢንቨስትመንት እድሎች ያሏት ሀገር መሆኗንም ተናግረዋል። በዚህም ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ኢንቨስት ማድረግ ለሚፈልጉ የታይላንድ ኩባንያዎች እና የንግድ ማህበረሰብ አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግላቸው አረጋግጠዋል። በኢትዮጵያ የታይላንድ አምባሳደር ጂሩሳያ ቢራናንዳ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያና ታይላንድ ረጅም ዘመናት ያስቆጠረ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት ናቸው። ይህን የሁለቱን ሀገራት መልካም የፖለቲካ ግንኙነት ወደ ጠንካራ የኢኮኖሚ አጋርነት እና ተጨባጭ የንግድ እድሎች መቀየር ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ የምትገኝ ቁልፍ የኢኮኖሚ ማዕከል መሆኗን ጠቁመው፤ ሀገሪቱ ያላት ሰፊና እያደገ የመጣ ገበያ፣ ስትራቴጂካዊ መገኛ፣ የበለጸገ የግብርና ሀብት፣ የልማት አጀንዳ እና እየተስፋፋ ያለው መሰረተ ልማት ለዓለም አቀፍ ባለሀብቶች ሰፊ የእድል የሚከፍት መሆኑን ገልጸዋል። ታይላንድ ከኢትዮጵያ ጋር የምታደርገው አጋርነት የሥራ እድል የሚፈጥር፣ የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር የሚያመጣ እንዲሁም ለጋራ ብልጽግና አስተዋፅኦ የሚያደርግ እንዲሆን እንደምትፈልግ አምባሳደሯ ተናግረዋል። የንግድ ማህበረሰቡ ከዛሬው መድረክ ወዳጅነትን ወደ አጋርነት፣ አጋርነትን ደግሞ ለጋራ ብልጽግና እንዲያውል ጥሪ አቅርበዋል።
በኦሮሚያ ክልል ሊከሰቱ የሚችሉ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመቋቋም በሚደረገው ጥረት ድጋፋችንን እናጠናክራለን - የሃይማኖት አባቶችና አባ ገዳዎች
Aug 29, 2026 92
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመከላከልና ፈጣን ምላሽ ለመስጠት እየተደረገ ያለውን እንቅስቃሴ በግንባር ቀደምትነት እንደሚደግፉ የሃይማኖት አባቶችና አባ ገዳዎች ገለጹ። በክልሉ አደጋን በራስ አቅም የመቋቋም አቅምን ለማጠናከርና የውጭ እርዳታ ጥገኝነትን ለመቀነስ የሚያስችሉ ዘርፈ ብዙ ጥረቶች በመደረግ ላይ ናቸው። በተለይም የተፈጥሮ ድርቅ፣ ጎርፍና ሌሎች ሰው ሠራሽ አደጋዎች በሚከሰቱበት ወቅት ፈጣንና ዘላቂ ምላሽ መስጠት የሚያስችል የውስጥ አቅም የመገንባት ተግባራት ተከናውነዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የሃይማኖት አባቶችና አባ ገዳዎች፤ ሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመከላከልና ፈጣን ምላሽ ለመስጠት የሚደረጉ እንቅስቃሴዎችን በመደገፍ የድርሻቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። አደጋዎችን በራስ አቅም የመቋቋምና የወገንን ችግር በጋራ የመፍታት ባህል የሕዝቡ የቆየ እሴት በመሆኑ፤ ይህንኑ ባህል ከማጠናከር አንጻር ውጤታማ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። በመሆኑም ማህበረሰቡን በማስተባበር፣ የበጎ ፈቃድ ስራዎችን በማጠናከርና ሀብት በማሰባሰብ ረገድ የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት በቁርጠኝነት እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። የሸገር ከተማ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ሰብሳቢ አባ አፈወርቅ ዮሐንስ በበኩላቸው፤ ለሚከሰቱ ሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች ምላሽ ለመስጠት ‘ቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ’ ያከናወናቸው ተግባራት የሚበረታቱ ናቸው ብለዋል። በተለይም ባለፉት አራት ዓመታት ለችግር የተጋለጡ ወገኖችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች በማቃለል ረገድ የላቀ ሚና እንደነበረው ጠቅሰዋል። ተቋሙ እያከናወናቸው ያሉትን ስኬታማ ተግባራት በመደገፍ በኩል የሃይማኖት ተቋማት አስፈላጊውን እገዛ ማድረግ እንዳለባቸውም አሳስበዋል። የ‘ቡሳ ጎኖፋ’ ስርዓት የሚበረታታ በመሆኑ የሃይማኖት ተቋማትን ጨምሮ የሁሉም አካላት ድጋፍ ሊደረግለት እንደሚገባ የገለጹት ደግሞ በሸገር ከተማ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ምክትል ሰብሳቢ ሼህ ሰይድ ሁሴን ናቸው። አሰራሩ ያለምንም ልዩነት ለችግር የተጋለጡ የህብረተሰብ ክፍሎችን በግንባር ቀደምትነት የሚደግፍ በመሆኑ፣ ማንኛውም በጎ ፈቃደኛ ዜጋና ተቋም አቅሙ የፈቀደውን ያህል ድጋፍ ሊያደርግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ‘ቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ’ ከገዳ ስርዓት የተቀዳና የኦሮሞ ሕዝብ በደስታም ሆነ በችግር ጊዜ በጋራ የሚረዳዳበት የቆየና የዳበረ ባህላዊ እሴት መሆኑን የገለጹት ደግሞ አባ ገዳ ወርቅነህ ተሬሳ ናቸው። ተቋሙ ለችግር የተጋለጡ የሕብረተሰብ ክፍሎችን በመደገፍና አደጋዎችን በመቋቋም ረገድ ያከናወናቸው ተግባራት ዜጎችን ተጠቃሚ እያደረጉ እንደሆነም ተናግረዋል። በኦሮሚያ ክልል የዲያስፖራ አባል የሆኑት አቶ ለሜሳ ከበደ በበኩላቸው፤ ‘ቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ’ አደጋዎች ሲከሰቱ በራስ አቅም ለመቋቋምና በቂ ምላሽ ለመስጠት የሚያደርገው ጥረት የሚበረታታ ነው ብለዋል። ይህን በራስ አቅም የመቆም ጥረት ከግብ ለማድረስም የዳያስፖራው ማህበረሰብ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት በቁርጠኝነት ለመወጣት ዝግጁ መሆኑንም አረጋግጠዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፎች የተመዘገበው ስኬትና የተገኘው ውጤት አበረታች ነው - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Aug 29, 2026 120
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፎች የተመዘገበው ስኬትና የተገኘው ውጤት አበረታች መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። የአማራ ክልል ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች የተሳተፉበት የ2018 በጀት ዓመት የመንግስትና የፓርቲ ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት እቅድ የትውውቅ መድረክ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ይገኛል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፎች የተመዘገበው ስኬትና የተገኘው ውጤት አበረታች ነው። እንደ ሀገር ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ በማካሄድ፣ በምጣኔ ሃብት፣ በመሰረተ ልማት ግንባታና በማህበራዊ ሴክተሮች ጭምር የሚጨበጥ ውጤት መጥቷል ብለዋል። የክልሉን ሰላምና ጸጥታ በማስጠበቅ ረገድም በቅንጅትና በትብብር በመስራት ህግን በማስከበርና የልማት ስራዎችን በማጠናከር የተመዘገበውን ስኬትም ለአብነት አንስተዋል። እንዲሁም ታጥቆ የሚንቀሳቀሰውን ፅንፈኛ ቡድን እና የፖለቲካ ፅንፈኝነትን በተደራጀ አግባብ አምርሮ በመታገል አስተሳሰቡን በማክሸፍ አበረታች ስራ መሰራቱን ተናግረዋል። በክልሉ የህግ የበላይነትን ከማረጋገጥ ባለፈም የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርታማነትን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶችን ተደራሽ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡና ኢኮኖሚያዊ መሳለጥን የሚያግዙ መሰረተ ልማትን በመዘርጋት፣ የኑሮ ውድነትን በማረጋጋት እና የስራ እድል በመፍጠርም አበረታች ስራ እንደተሰራ አረጋግጠዋል። መልካም አስተዳደርን በማስፈን፣ ሙስናና ብልሹ አሰራርን በመታገል፣ ውስጣዊ የገቢ አቅምን በማሳደግ በኩልም የተሻለ አፈፃፀም ተመዝግቧል ነው ያሉት። በአጠቃላይ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ሰላምን ከማጽናት ጎን ለጎን የክልሉን ህዝብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች መከናወናቸውን አብራርተዋል። የተመዘገቡ ሁለንተናዊ ውጤቶች የበለጠ ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ጠቅሰው፤ ነገር ግን አሁንም ያልተፈቱና ያደሩ የፀጥታ ችግሮችን በተሻለ ቅንጅት መፍታት ይገባል ብለዋል። በአዲሱ በጀት ዓመት የህዝቡን የልማት ተጠቃሚነት ከማሳደግ ባለፈ የገቢ መሰረትን በማስፋት፣ መልካም አስተዳደርን በማስፈን፣ የህግ የበላይነትን በማረጋገጥ በላቀ ቁርጠኝነት አመራሩ ምስራት እንዳለበት አሳስበዋል። በመድረክ የጋራ መግባባትና ግንዛቤ በመፍጠር የመንግስትና የፓርቲ ስራዎችን በውጤታማነት መምራት እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ''አርቆ ማየት አልቆ መስራት'' በሚል መሪ ሃሳብ የተጀመረው መድረክ ከነሐሴ 23 እስከ 27/2018 ዓ/ም የሚቆይ ሲሆን በመድረኩ በየደረጃው የሚገኙ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛል።
የኢትዮጵያ አዲሱ የቱሪዝም ከፍታ!
Aug 29, 2026 112
የኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ከሀገሪቷ ልዩ ፀጋዎች መካከል በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። ሀገሪቱ ያሏት ጉምቱ ታሪክ፣ ብዝሃ ባህል እና ልዩ የቱሪዝም መዳረሻዎች ለአፍሪካ ስልጣኔ ያላትን ታላቅ ድርሻ የሚያመላክቱ ናቸው። ከላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አንስቶ እስከ አክሱም ሀውልትና የጁገል ግንብ ድረስ ያሉት ቅርሶች የኢትዮጵያን የታሪክ ጥልቀት እና የባህል ትሩፋቶች በግልጽ ያሳያሉ። እነዚህ ታሪካዊ ሀብቶች በአሁኑ ወቅትም የውጭ ጎብኚዎች፣ ተመራማሪዎች እና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ቀልብ መሳባቸውን ቀጥለዋል። ከታሪክ ሀብቶቿ ባለፈም ማራኪው የመልክዓ ምድር አቀማመጥ፣ ብቅ ያሉ የዱር እንስሳቶች እና የዜጎች እንግዳ ተቀባይነት የአኗኗር ዘይቤ ለዘርፉ ዕድገት ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ። መንግስት ቱሪዝምን እንደ አንድ ዋነኛ የኢኮኖሚ ምሰሶ በመውሰድ ስትራቴጂካዊ የልማት ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል። በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተቀረጹት የ"ገበታ ለሸገር"፣ "ገበታ ለሀገር" እና "ገበታ ለትውልድ" ፕሮጀክቶች የሀገሪቱን እምቅ የቱሪዝም ሀብት ከማውጣት ባለፈ የገቢ መጠንን በማሳደግ ረገድ ጉልህ ለውጥ እያስመዘገቡ ነው። ከዚህም መካከል በሶማሌ ክልል በደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያ በዋቢ ሸበሌ ወንዝ ዳርቻ ተገንብቶ በቅርቡ የተመረቀው እና የ"ገበታ ለትውልድ" አካል የሆነው የሸበሌ ሪዞርት አንዱ ማሳያ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምርቃቱ ወቅት እንደገለጹት፣ ሪዞርቱ ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ የገባነውን ቃል በተግባር ያረጋገጠ የምስራቁ የሀገራችን ክፍል ትልቅ ማሳያ ሥራ ነው። ይህ ስራ በታችኛው የዋቢ ሸበሌ ተፋሰስ አካባቢ ለአካባቢው ማህበረሰብ የስራ እድል የፈጠረና የክልሉን የቱሪዝም ገጽታ የቀየረ ነው። በተጨማሪም በመዲናዋ አዲስ አበባ የተገነቡት የወዳጅነት አደባባይ፣ አንድነት ፓርክ፣ ሳይንስ ሙዚየም እና አብርሆት ቤተ-መጻሕፍት አዳዲስና ተመራጭ የከተማ ቱሪዝም (Urban Tourism) መዳረሻዎች ሆነዋል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በዋና ከተማዋ የተከናወነው ሰፊው የኮሪደር ልማት ሥራ የአዲስ አበባን መልክ በአዲስ ሁኔታ በመግለጥ፣ ከተማዋን ለሰው ልጅ ምቹ፣ ውብ እና የጎብኚዎች ዓይን ይበልጥ የሚያርፍባት የቱሪስት ማዕከል አድርጓታል። ከታሪካዊ ቅርሶች ጥበቃ አንጻርም እድሳት የተደረገላቸው ብሔራዊ ቤተ መንግስት (ኢዮቤልዩ)፣ የጎንደር የአፄ ፋሲል አብያተ መንግስታት፣ የጅማ አባጅፋር ቤተመንግስት እና የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ለዘርፉ መነቃቃት የጎላ አበርክቶ እያበረከቱ ይገኛሉ። ከዚሁ ጋር ተያይዞ፣ በቅርቡ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡት የጌዴኦ ባህላዊ መልክዓ ምድር እና የባልካሌ ውብ ተፈጥሮአዊ ጥንታዊ ቅርሶች የኢትዮጵያን የቱሪዝም ካርታ ይበልጥ አበልጽገውታል። ይህ ዓለም አቀፋዊ እውቅና የሀገሪቱን የባህል እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ጥረት ማሳደጉ ብቻ ሳይሆን፣ ወደ እነዚህ አካባቢዎች የሚመጡ የውጭ እና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎችን ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ በማሳደግ የቱሪዝም ገቢን ለማሳደግ አስችሏል። በሌላ በኩል፣ የቱሪዝም ዘርፉን ስኬት ዘላቂ ለማድረግ የአቪዬሽን እና የእንግዳ ተቀባይነት (Hospitality) አገልግሎቶች ዲጂታላይዝ መሆናቸው ጉልህ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ መዳረሻ ማብዛት፣ የኤሌክትሮኒክስ ቪዛ (e-Visa) አሰጣጥ መዘመኑ እና ወደ ተለያዩ የመዳረሻ አካባቢዎች የሚደረጉ የትራንስፖርት አማራጮች መቃናታቸው ጎብኚዎች ያለ ምንም እንግልት ሀገሪቱን እንዲጎበኙ መንገድ ከፍቷል። ይህም ሀገሪቱ በኮንፈረንስ ቱሪዝም ለአፍሪካ እና ለዓለም አቀፍ ስብሰባዎች ተፈላጊ ማዕከል እንድትሆን አስችሏታል። በተጨማሪም የዲጂታል ቱሪዝም ፕሮሞሽን እና የቅርሶች ጥበቃ ስራዎች በዘመናዊ ቴክኖሎጂ መደገፋቸው ለዘርፉ አዲስ ምዕራፍ አጎናጽፎታል። በማህበራዊ ሚዲያ እና በዲጂታል አማራጮች የሚሰሩ ማስተዋወቂያዎች የኢትዮጵያን ገጽታ ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ በአዲስ መልክ አስተዋውቀዋል። እነዚህ የተቀናጁ የልማት፣ የጥበቃ እና የማስተዋወቅ ስራዎች ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ ብቻ ሳይሆን በመላው አህጉር ቀዳሚ የቱሪዝም መዳረሻ የመሆን ራዕይዋን በተግባር እያረጋገጡት ይገኛሉ። ይህንን የመንግስት ጥረት ተከትሎም ከባለሀብቶች እንዲሁም ከዓለም አቀፍ የዘርፉ ተዋንያን የሚመጣው ተሳትፎና የኢንቨስትመንት ፍላጎት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መጥቷል። በአጠቃላይ እነዚህ ዘመናዊ መሠረተ ልማቶች፣ የታሪካዊ ቅርሶች ጥገና እና የተፈጥሮ መስህቦች ጥምረት የኢትዮጵያን የቱሪዝም ዘርፍ ለኢኮኖሚ እድገት እና ለዘላቂ ልማት ያለውን ድርሻ ወደ ላቀ ደረጃ እያሳደጉት ይገኛል።
ኢትዮጵያ እንደ ሕዳሴ ግድብ ሁሉ የባሕር በር ጥያቄዋንም ማሳካት የምትችል ታላቅ ሀገር ናት - ኡስታዝ ጀማል በሽር
Aug 28, 2026 387
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ እንደ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ሁሉ የባሕር በር ጥያቄዋን ማሳካት የምትችል ታላቅ ሀገር መሆኗን የዓባይ ንጉሶች ሚዲያ ባለቤት ኡስታዝ ጀማል በሽር ተናገሩ። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ የውሃ ሀብቶቿን በራሷ አቅም አልምታ መጠቀም እንደምትችል ያሳየ መሆኑንም ገልጸዋል። ኡስታዝ ጀማል በሽር፤ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ቀጣናውን በኤሌክትሪክ ኃይል በማስተሳሰር ትብብርን ከማጠናከር አኳያ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከተፋሰሱ ሀገራት ጋር ያላት ትብብር በጋራ ተጠቃሚነትና ልማት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ታላቁ የህዳሴ ግድብ በተግባር ማሳየቱንም ነው የጠቆሙት። ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን እንዳትጠቀም የሚከለክላት ማንም አካል እንደሌለ ጠቅሰው የሀገሪቷ የመልማት መብት ዓለም አቀፍ ህጎችና መርሆዎችን ያከበረ እንደሆነም ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን ተጠቅማ በቀጣይ ለማከናወን ያሰበቻቸው ስራዎች ሀገሪቷን ወደ ተሻለ ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ ናቸው ሲሉም ተናግረዋል። እየተጠናቀቁ ያሉ የመስኖ ግድቦች፣ አብዛኛው ስራ የተጠናቀቀው የኮይሻ ኤሌክትሪክ ማመንጫ ፕሮጀክትና ሌሎች ስራዎች የኢትዮጵያን የልማት ውጥን እውን የሚያደርጉ ናቸው ብለዋል። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ በሁሉም መስኮች ያሰበቻቸውን እያሳካች መሆኑን ጠቅሰው፤ በከተማ ልማት፤ ቱሪዝም እንዲሁም በምክክር የመግባባት ዴሞክራሲን በመገንባት ረገድ ውጤታማ ስራ እያከናወነች ስለመሆኑ አብራርተዋል። አሁን ደግሞ የኢትዮጵያ የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ የሆነውን የባሕር በር ጥያቄ በይፋ አንስታለች ነው ያሉት። የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ የህልውና ጉዳይ እና በፍትሃዊነት የመልማት ጥያቄ መሆኑን በማንሳት፤ ይህንን ማሳካት ደግሞ የትውልዱ የማይቀር እውነት ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ የባህር በር ማግኘቷ አይቀሬ መሆኑን ጠላት ሳይቀር እየመሰከረው ያለው ሃቅ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ እንደ ሕዳሴ ግድብ ሌሎች ታላላቅ ፕሮጀክቶች ሁሉ የባሕር በር ጥያቄዋንም ማሳካት የምትችል ታላቅ ሀገር ስለመሆኑም ኡስታዝ ጀማል ተናግረዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በመኸር እርሻው ከ72 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቅባት እህሎች እየለማ ነው
Aug 28, 2026 189
አምቦ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን በመኸር እርሻው ከ72 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቅባት እህሎች በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገልጿል። ምዕራብ ሸዋ ዞን ለተለያዩ የሰብል አይነቶች ተስማሚ የሆነ የአየር ንብረት እና ለም አፈር ያለው አካባቢ ነው። ዞኑ ከዋና ዋናዎቹ የጥራጥሬ እና የእህል ዘሮች ባሻገር፣ እንደ ኑግ፣ ተልባ፣ ሰሊጥ እና የጎመን ዘር ያሉ የቅባት እህሎችን በማምረት በኩል ከፍተኛ አቅም አለው። በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የአዝእርት ልማት ባለሙያ አቶ በላይ በቀለ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በ2018/19 የምርት ዘመን ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውን የቅባት እህሎች በማልማቱ ስራ ላይ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል። ከለማው ሰፊ መሬት ውስጥ 40 ሺህ 665 ሄክታሩ በሰሊጥ የተሸፈነ ሲሆን፣ ቀሪው መሬት ደግሞ በኑግ፣ በተልባ፣ በጎመን ዘር እና በለውዝ መልማቱን ባለሙያው ገልጸዋል። ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግም በግብርና ምርምር ማዕከላት የተሻሻሉ የቅባት እህሎች ለአርሶ አደሩ ተሰራጭተው ጥቅም ላይ እየዋሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። የቅባት እህል ልማቱ የምግብ ዘይት እጥረትን ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አቶ በላይ ተናግረዋል። በቅባት እህሎች ልማት 88 ሺህ 761 የዞኑ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ ሲሆን፣ አሁን እየለማ ካለው መሬት 653 ሺህ 535 ኩንታል ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ ጠቁመዋል። በልማቱ ከተሳተፉት መካከል የአምቦ ወረዳው አርሶ አደር ፈይሳ በቀለ በሰጡት አስተያየት፣ በግማሽ ሄክታር መሬት ላይ ኑግ እንዲሁም በሌላ ግማሽ ሄክታር ላይ ተልባ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል። ካለሙት መሬት ጥሩ ምርት እንደሚጠብቁ በመግለጽ፣ በአሁኑ ወቅትም ጠንካራ የአረምና የተባይ አሰሳ ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን አስረድተዋል። ሌላው የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር አለማየሁ በሬቻ፣ በመኸር እርሻው በግማሽ ሄክታር ማሳቸው ላይ ተልባና ጎመን ዘር መዝራታቸውን በመግለጽ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል። የቅባት እህል ምርት በገበያ ላይ ከፍተኛ ተፈላጊነት ያለው በመሆኑ፣ ልማቱን ይበልጥ የማስፋፋት እቅድ እንዳላቸው አስረድተዋል። አርሶ አደሮቹ በግብርና ባለሙያዎች አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገላቸው በመሆኑ፣ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። በምዕራብ ሸዋ ዞን ባለፈው መኸር ከለማው ከ69 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ከ623 ሺህ ኩንታል በላይ የቅባት እህል ምርት መገኘቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።
የህብረት ስራ ማህበራት ሪፎርም ለክልሉ ኢኮኖሚያዊ እድገት ወሳኝ ድርሻ አለው-ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር)
Aug 28, 2026 98
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል እየተከናወነ ያለው የህብረት ስራ ማህበራት ሪፎርም ለክልሉ አጠቃላይ ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና ለአምራቹ ተጠቃሚነት ወሳኝ ድርሻ እያበረከተ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) ገለጹ። በደቡብ ጎንደርና በምዕራብ ጎጃም ዞኖች ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ሁለት የዘር ብዜትና ግብይት ህብረት ስራ ማህበራት ዩኒዮኖችን የማዋሃድ ስራ ዛሬ ተካሂዷል። የክላስተሩ አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ዩኒዮኖቹን ወደ አንድ የማዋሀድ ስራ የተካሄደው በሁሉም መስክ አቅም ፈጥረው የተጣለባቸውን ተልእኮ በተሻለ መልኩ እንዲወጡ ለማድረግ ነው። የጉና እና የዕድገት የዘር ብዜት የህብረት ስራ ማህበራት ዩኒየኖች መዋሃዳቸው ጠንካራ ኢኮኖሚያዊ አቅም በመፍጠር የአርሶ አደሩን የዘር አቅርቦት ችግር ለመፍታት የሚያስችል ነው ብለዋል። የተዋሃዱት ዩኒየኖች ‘‘አንድነት የዘር ብዜትና ግብይት ኃላፊነቱ የተወሰነ የህብረት ስራ ማህበራት ዩኒየን'' ተብለው የተቋቋሙ ሲሆን የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የጎላ ድርሻ ይኖራቸዋል ብለዋል። በተለይ ከበቆሎ ምርጥ ዘር በተጨማሪ የተለያዩ የሰብል ዘሮችን በጥራት አባዝተው ለአርሶ አደሩ እንዲያቀርቡ ድጋፍና ክትትል ይደረግላቸዋል ብለዋል። ባለፉት ሁለት ዓመታት በተካሄደ የሪፎርም ስራዎች 388 ሁለገብ ህብረት ስራ ማህበራትን 141 ሆነው እንዲዋሃዱ በማድረግ ፋይናንሻል አቅማቸውና የአመራር ብቃታቸውን ጠንካራ እንዲሆን ተደርጓል ያሉት ደግሞ የክልሉ ህብረት ስራ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጌትነት አማረ ናቸው። እንዲሁም 19 የህብረት ስራ ማህበራት ዪኒየኖችን ወደ 9 ዩኔዮኖች እንዲዋሃዱ በማድረግ የፋይናንስ አቅማቸው እንዲጠናከርና በገበያ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የማድረግ ስራ መከናወኑን ኮምሽነሩ አመልክተዋል። በዛሬው ዕለትም በዘር ብዜት ተሰማርተው ሲሰሩ የቆዩትን የ''ጉናና የዕድገት ዘር ብዜትና ግብይት ህብረት ስራ ማህበራት ዩኒየኖች' ውህደት መፈፀማቸው ለዘርፉ ዕድገት ወሳኝ ድርሻ እንዳለው አመላክተዋል። በቀጣይም ኮሚሽኑ ሌሎች ህብረት ስራ ማህበራትና ዩኒዮኖችን በማሰባሰብ ጠንካራ ሆነው እንዲወጡ የሪፎርም ስራውን አጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት። የአንድነት የዘር ብዜትና ግብይት ህብረት ስራ ማህበራት ዩኒዮን የቦርድ ሰብሳቢ አርሶ አደር ደሴ ተረፈ፤ ውህደቱ አሰራርን በማዘመንና ምርትና አገልግሎታቸውን ተደራሽ በማድረግ የአርሶ አደርን ተጠቃሚነት የሚያሳድግ ነው ብለዋል። በቀጣይም በክልሉ ከ32 ሺህ የሚበልጡ ህብረት ስራ ማህበራትንና 61 ዩኒዮኖችን ለማዋሃድ እንደሚሰራም ነው የጠቀሱት።
የአፍሪካን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠን የድንበር ላይ አሰራሮችን የሚያሳልጥ ተጨባጭ እርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል - የአፍሪካ ሕብረት
Aug 28, 2026 302
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠን የሀገራትን የድንበር ላይ አሰራሮችን የሚያሳልጥ ተጨባጭ እርምጃ መውሰድ እንደሚያስፈልግ የአፍሪካ ሕብረት ገለጸ። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽንና የዓለም ባንክ ያተዘጋጁ''አፍሪካን ማቀናጀት፤ ከተበታተኑ ትስስሮች ወደ ኢኮኖሚያዊ ማዕከላት'' የተሰኘ አዲስ አህጉራዊ የጥናት ሪፖርት ይፋ ሆኗል። የጥናት ሪፖርቱም የአፍሪካን ከቀረጥ ነፃ የንግድና የምርት ትስስር በማጠናከር የአህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣናን በዘመናዊ መሠረተ ልማት በማስደገፍ የአህጉሪቱን ኢኮኖሚ ውህደት ማጠናከር እንደሚገባ አመላክቷል። በሕብረቱ ኮሚሽን የኢኮኖሚ ልማት፣ ንግድ፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪና ማዕድን ኮሚሽነር ፍራንሲስካ ታቾፕ ቤሎቤ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ አፍሪካ በተሰናሰለ አሠራርና መሠረተ ልማት የሚመራ የኢኮኖሚ ውህደትን ማሳለጥ ያስፈልጋታል። ይህም የአህጉሪቱን የተበታተነ የገበያና የግብይት ሥርዓት ውጤታማነት በማሻሻል አፍሪካን የጠንካራ ኢኮኖሚ ማዕከል ለማድረግ ቁልፍ ሚና እንደሚኖረው ገልጸዋል። የአፍሪካ ኢኮኖሚ ውህደት በሚፈረሙ ስምምነቶች ብቻ አይሳካም ያሉት ኮሚሽነሩ፤ የአህጉሪቱን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠንም የሀገራትን የድንበር አሠራሮችን የሚያሳልጥ እርምጃ መውሰድ ያስፈልጋል ብለዋል። የአፍሪካን አህጉራዊ የነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት የትብብር ማዕቀፍ በውጤታማነት በመተግበር የአህጉሪቷን ዜጎች የጋራ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ንግድና ኢንቨስትመንትን ማፋጠን እንደሚገባ ተናግረዋል። ለዚህም የአህጉሪቷን አባል ሀገራት የድንበር ላይ መተላለፊያ፣ ጉምሩክ፣ ታሪፍና የዲጂታል ክፍያ እንቅፋቶችን ማስወገድ የሚያስችል ቀልጣፋ አሠራር መዘርጋት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። የአህጉሪቷን የኢኮኖሚ ውህደትን ለማሳለጥ የሚደረጉ ጥረቶችም ጥሬ ዕቃን ከመላክ የተላቀቀ የኢንዱስትሪ፣ የኃይልና የትራንስፖርት እሴት ሰንሰለት የሚያጎለብት ነው ብለዋል። ይህም የበለፀገችና የተሳሰረች አፍሪካን የመገንባት የአጀንዳ 2063 ራዕይን በማሳካት የአፍሪካዊያንን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያሻሽል የኢኮኖሚ ምኅዳር መፍጠር እንደሚያስችል ገልጸዋል። የዓለም ባንክ የምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ ቀጣናዊ ምክትል ፕሬዝዳንት ንዲያሜ ዲዮፕ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአፍሪካ የተቀናጀ መሠረተ ልማትና የሎጂስቲክስ ሥርዓት ለኢኮኖሚ ውህደት አስፈላጊ ነው ብለዋል። የአህጉሪቷን የኢኮኖሚ ውህደት ለሚያሳልጥም የተቀናጀ የመሠረተ ልማት አቅርቦትን በመገንባት የአርሶ አደሩን፣ የኢንዱስትሪና ገበያን በቀጥታ የሚያገናኝ ምኅዳር መፍጠር እንደሚገባ ገልጸዋል። የመሠረተ ልማቶች ትስስር አህጉራዊ የግብርና ገበያዎችንና የፋብሪካ ምርቶችን በማጠናከር ለአፍሪካውያን ሰፊና ዘላቂ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥርም ጠቅሰዋል። የዓለም ባንክ የንግድ እንቅፋቶችን በመቀነስ፣ የድንበር ተሻጋሪ አሠራሮችን በማቃለል የአፍሪካን እውነተኛ የኢኮኖሚ ውህደትና የሥራ ዕድል በሚፈጥሩ መሠረተ ልማቶች ላይ ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
በዞኑ 217 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ለምቷል
Aug 28, 2026 73
ገንዳ ውኃ፣ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን በ217 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውል የአኩሪ አተር ሰብል እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተያዘው የመኸር ወቅት የኢንዱስትሪ ጥሬ ዕቃ ፍላጎትን ለማሟላትና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። የግብርናው ዘርፍ ለኢኮኖሚ እድገት ያለውን የጎላ አበርክቶ ለማሳደግ ምርታማነትን መጨመር አስፈላጊ በመሆኑ፣ በቂ የግብርና ግብዓት ለአርሶ አደሩ በወቅቱ እንዲሰራጭ መደረጉንም ተናግረዋል። በአኩሪ አተር ልማቱ 60 ሺህ የሚደርሱ አርሶ አደሮችና ከ600 በላይ አልሚ ባለሃብቶች የተሳተፉ ሲሆን፤ ከልማቱ ከ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ አስረድተዋል። ጥራቱ የተጠበቀ ምርት ለማግኘት ከዘር ወቅት ጀምሮ በቅድመና ድህረ-ምርት አያያዝ ላይ ሰፊ ክትትልና ቁጥጥር የማድረግ ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ኃላፊው አመልክተዋል። የምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ገብሬ መልኬ በበኩላቸው፤ በተያዘው የመኸር ወቅት ከ60 ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ማልማት መቻላቸውን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪዎች መስፋፋትና የገበያ ሁኔታው መሻሻል ለአኩሪ አተር ሰብል ልማት ይልጥ ትኩረት እንዲሰጡ እንዳደረጋቸውም ተናግረዋል። በወረዳው የኮረደም እርሻ ጣቢያ አልሚ አርሶ አደር ምህረቴ ምኒልክ፤ ምርታማነትን በሚያሳድጉ ቴክኖሎጂዎች በመታገዝ አኩሪ አተር እያለሙ መሆኑን ገልጸዋል። ከግብርና ባለሙያዎች የሚደረግላቸው ሙያዊ ድጋፍና የሚቀርቡ የግብርና ግብዓቶች የሰብሉ ቡቃያ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንዲገኝ ማስቻሉንም አክለዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን ባለፈው የምርት ዘመን ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአኩሪ አተር ለምቶ 5 ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ምርት መገኘቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የታይላንድ–አፍሪካ ኢኒሼቲቭ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ትብብርን ለማጠናከር አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው
Aug 28, 2026 304
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ የታይላንድ–አፍሪካ ኢኒሼቲቭ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ትብብርን ለማጠናከር አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው ሲሉ የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉአንግኬትኬኦ ገለጹ። የታይላንድ-አፍሪካ የትብብር መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉአንግኬትኬኦ በመድረኩ ላይ ባደረጉት ንግግር ታይላንድ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ሁለንተናዊ ግንኙነት ወደ ላቀ የስትራቴጂያዊ አጋርነት ለማሳደግ የሚያስችል አዲስ ማዕቀፍ ይፋ አድርገዋል። ሚኒስትሩ በዚሁ መድረክ ላይ የጉብኝታቸው ዋነኛ መነሻ ኢትዮጵያ እና ናይጄሪያ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በአራት ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ የተመሰረተው ይህ የትብብር ማዕቀፍ በተለይም ከአፍሪካ ኅብረት እና ከምዕራብ አፍሪካ ሀገራት የኢኮኖሚ ማህበረሰብ (ECOWAS) ጋር ያለውን ተቋማዊ ትብብር በይበልጥ ለማጠናከር ያለመ ነው። በተጨማሪም በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና እና በደቡብ ምሥራቅ እስያ ሀገራት ማኅበር (ASEAN) መካከል ጠንካራ የኢኮኖሚ ድልድይ ለመፍጠር ታስቧል። ዓላማውን ከዳር ለማድረስም የታይላንድ የንግድ ልዑክ በአዲስ አበባ ከኢትዮጵያ የመንግሥት እና የግል ዘርፍ ተወካዮች ጋር በመገናኘት የንግድ ማኅበረሰቡን የሚያስተሳስር ውይይት እንደሚያደርግ ተገልጿል። በሌላ በኩል ታይላንድ የደቡብ-ደቡብ ትብብርን ለማጎልበት ለቀጣዮቹ ሦስት ዓመታት የሚተገበር እና ሦስት ሚሊዮን ዶላር በጀት የተመደበለት አዲስ የድርጊት መርሐ ግብር ይፋ አድርጋለች። መርሐ ግብሩ በዋናነት በግብርና፣ በምግብ ዋስትና እና በቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ ትኩረት የሚያደርግ ሲሆን፣ በተለያዩ የአፍሪካ አካባቢዎች የግብርና ማሠልጠኛ ማዕከላትን ለማቋቋም ይውላል። በፈረንጆቹ 2028 የደቡብ ምሥራቅ እስያ ሀገራት ማኅበር ሊቀመንበርነትን የምትረከበው ታይላንድ፣ በማኅበሩ እና በአፍሪካ ኅብረት መካከል በምግብ እና ኃይል ዋስትና እንዲሁም በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ዙሪያ ያለውን ዘርፈ ብዙ ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር እንደምትሠራ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አረጋግጠዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርናን በማዘመን የተገኙ ስኬቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Aug 28, 2026 84
ዱራሜ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርናን በማዘመን የተገኙ ስኬቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ ። "የተቀናጀ የግብርና ትጋት ለተመጣጠነ ምርታማነት" በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ ክልላዊ የግብርና ሴክተር የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና የ2019 ዕቅድ ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በዱራሜ ከተማ ተካሂዷል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኡስማን ስሩር በዚህ ወቅት እንዳሉት በክልሉ ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰሩ ሥራዎች ስኬት ተመዝግቧል። የዘርፉን ስኬታማነት ይበልጥ ለማሳደግ ለቴክኖሎጂና ለሰው ሀይል ልማት ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ መቻሉንም ጠቁመዋል። ይህም የአርሶ አደሩን የምግብ ሉአላዊነትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ ባለፈ ገበያን ለማረጋጋት እያገዘ በመሆኑ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል። የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ አበራ ወንድሙ በበኩላቸው በዞኑ ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተሰራው ሥራ ውጤት አስገኝቷል። አርሶ አደሩ በኩታ ገጠም የማልማት ልምዱን ከማስፋፋት ባለፈ የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀሙ ማደጉ በበቆሎ ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግ መቻሉን አስረድተዋል። በዘርፉ እየተመዘገቡ የሚገኙ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል የአመራሩ፣ የግብርና ባለሙያውን እና የአርሶ አደሩ ቅንጅታዊ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አቶ አበራ ገልጸዋል። የከምባታ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ ተሾመ ሄራሞ በበኩላቸው በዞኑ ከሰብል ልማት በተጨማሪ የቡና እና የቅመማ ቅመም ልማት እየተስፋፋ ነው። ለአብነትም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ12ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ዝንጅብል መልማቱንና ለአርሶ አደሩም የገበያ ትስስር መፈጠሩን አንስተዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርት በማምረት ሚናቸው እያደገ መጥቷል
Aug 28, 2026 90
አርባ ምንጭ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርት በማምረት ያላቸው ሚና እያደገ መምጣቱ ተገለጸ። "የኢትዮጵያን ይግዙ" በሚል መሪ ሃሳብ ክልል አቀፍ የንግድ ባዛር እና ኤግዚቢሽን ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ ተከፍቷል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ አቶ ተፈሪ አባተ እንደገለጹት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን ተከትሎ በክልሉ የሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርቶችን በማምረት በኩል ያላቸው ሚና እያደገ መጥቷል። በክልሉ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄና በገጠር ኢንዱስትሪያላይዜሽን የተቀናጀ ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፣ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ለማጠናከር የኤክስፖርት ምርት አቅርቦትን በጥራትና በብዛት ማሳደግ እንደሚገባ ጠቁመዋል። የክልሉ መንግስት የአምራች ኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ማነቆ የሆኑ ችግሮችን በመፍታት የተሻለ እመርታ ለማስመዝገብ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሠራ መሆኑንም ተናግረዋል። ህጋዊ የንግድ ስርአትና ተወዳዳሪነትን በማስፈን የክልሉን ኢኮኖሚ ለማረጋጋት በተደረጉ ጥረቶች ለውጥ እየተመዘገበ መሆኑንም አቶ ተፈሪ አስረድተዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም የሀገር ውስጥ እና የውጭ ገበያ ድርሻን ከማላቅ ባለፈ ህገ-ወጥነትን በመከላከል ጤናማ የገበያ ሰንሰለት ለመፍጠር ትኩረት መሰጠቱን አቶ ተፈሪ አስታውቀዋል። የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ሃላፊ ሰናይት ሰለሞን በበኩላቸው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዋና ዋና ሀገራዊ ተልዕኮዎች የተሻለ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል። በተለይ 22 መካከለኛ እና 134 አነስተኛ ኢንዱስትሪዎች በሙሉ አቅም ማምረት እንዲችሉ መደረጉ ክልላዊ የማምረት አቅምን 63 በመቶ አድርሷል ብለዋል። በክልሉ የሚገኙ ከፍተኛ፣ መካከለኛና አነስተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ከውጭ ምርቶች ጥገኝነት የሚያላቅቁ ተኪ ምርቶችን በስፋት ማምረት እንደቻሉም ገልጸዋል። በክልሉ በሚገኙ 105 የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች የግብርና፣ የእንስሳትና እንስሳት ተዋጽኦ እንዲሁም የኢንዱስትሪ ምርቶች አቅርቦትን በማሻሻል የገበያ ማረጋጋት ሥራ ተሠርቷል ብለዋል። የአርባ ምንጭ "ኤሊያና ጋርሜንት" ምክትል ሥራ አስኪያጅ ኤርሚያስ ደማ እና በወላይታ ሶዶ "ሰላሙ የቆዳና የቆዳ ውጤቶች ማህበር" ሰብሳቢ ዮናስ ቶማስ በንግድ ባዛርና ኤግዚቪሽኑ መሳተፋቸው ምርቶቻቸውን በማስተዋወቅ የገበያ ሰንሰለት ለመፍጠር ምቹ አጋጣሚ ይፈጥራል ብለዋል። የሀገር ውስጥ ምርቶች በጥራትም ሆነ በንድፍ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እየሆኑ በመምጣታቸው ማህበረሰቡ የሀገሩን ምርት የመጠቀም ልምዱን ማሳደግ እንዳለበት አመልክቷል። ክልል አቀፍ የንግድ ባዛርና ኤግዚቢሽኑ ከዛሬ ጀምሮ ለተከታታይ ስድስት ቀናት የሚቆይ ሲሆን የተለያዩ አምራቾች፣ አስመጪዎች፣ ላኪዎች እና ኢንዱስትሪያሊስቶች ምርቶቻቸውን በማቅረብ እየተሳተፉ ነው።
በምስራቅ ወለጋ ዞን የክረምት እርሻ እና የልማት ኢንሼቲቮች አፈጻጸም በጥሩ ደረጃ ላይ ይገኛል
Aug 28, 2026 94
ነቀምቴ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ) :-በምስራቅ ወለጋ ዞን የ2018/2019 የምርት ዘመን የክረምት እርሻ እናየልማት ኢንሼቲቮች አፈጻጸም በጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት ምክትል ሀላፊ ደረጄ ብርሃኑ(ዶ/ር) በምርት ዘመኑ የተሻለ ምርት ለማግኘት ከአቅርቦት ጀምሮ በተሰራ ስራ ከታቀደው በላይ ማሳ በዘር ተሸፍኖ የሰብል እንክብካቤ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በዚህም 801 ሺህ 185 ሄክታር መሬት ለማረስ ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ 831 ሺህ 816 ሄክታር በማረስ ከታቀደው በላይ 103.8 በመቶ ማሳካት መቻሉን ያሳያል። አርሶ አደሩ የግብርና ፓኬጆችን በመጠቀም ምርታማነቱን እንዲያሳድግ በተጀመረው የሙሉ ፓኬጅ ስራም፤ 210 ሺህ 635 ሄክታር በሙሉ ፓኬጁ ማረስ መቻሉን ጠቁመዋል። በልማት ኢኒሼቲቭ በተከናወኑ የክረምት ሰብሎች ስራም በቆሎ 134 በመቶ፣ ቦሎቄ 122 በመቶ፣ ኦቾሎኒ 106 በመቶ፣ እንዲሁም ማሽላና ስንዴ እያንዳንዳቸው 103 በመቶ በማረስ ከዕቅድ በላይ መፈጸም ተችሏል ብለዋል። በሚገኘው የተሻለ ምርትም የራስ ፍጆታን ከመሸፈን ባለፈ ምርቱን ለማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ መታቀዱን ገልጸዋል። በኩታገጠም እርሻም 642 ሺህ 62 ሄክታር መሬት ታርሶ በዘር መሸፈኑን አስታውሰው፤ በዘርፉ በየጊዜው በተሰራው የግንዛቤ ማስጨበጫ እና በተደረገው የቅርብ ክትትል ለውጥ መመዝገቡንም አብራርተዋል። በሌላ በኩል ከግብርና ግብዓቶች አቅርቦት ጋር ተያይዞ፣ ወቅቱን የጠበቀ የዘር እና የማዳበሪያ አቅርቦት ለተጠቃሚዎች እንዲደርስ መሰራቱን ዶክተር ደረጄ ገልጸዋል። የተዘራው ሰብል ለተፈለገው ምርታማነት እንዲበቃና ከአረም ጥቃት እንዲጠበቅ የአረም መድኃኒት አቅርቦት እና አጠቃቀም ላይ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም ዶክተር ደረጄ አክለው ገልጸዋል። በተመሳሳይ በሰብል ጥበቃ በተለይም ተባይ ቁጥጥርም 226 ሺህ 326 ሄክታር ተፈትሾ 42 ሺህ 823 ሄክታር ላይ የመቆጣጠር ሥራ ተከናውኗል ብለዋል። በዞኑ የልማቱ ተሳታፊ አርሶ አደሮች በበኩላቸው የግብርና እና ሌሎች የልማት ኢንሼቲቮችን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ተግተው እየሰሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በዞኑ የዲጋ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ሰንበቶ ኢቲቻ በኩታገጠም እርሻ የተለያዩ ሰብሎችን እያለሙ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ባላቸው ከሁለት በላይ ሄክታር መሬትም የተሻለ ምርት ለማግኘት የግብርና ሜካናይዜሽኖችን እየተጠቀሙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሌላኛው አርሶ አደር አዲሱ ግዛው በየደረጃው የሚገኙ የግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ እና ክትትል እያደረጉላቸው እንደሚገኙ ተናግረዋል። ከራሳቸው ጥረት ጋር በባለሙያዎቹ በመታገዝም የተሻለ ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውን ገልጸዋል።
ተግባራዊ የተደረጉ የግብርና ቴክኖሎጂና የምርጥ ዘር አቅርቦቶች የአርሶ አደሩን ውጤታማነት እያሳደጉ ናቸው
Aug 28, 2026 277
ሮቤ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፡- ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ተግባራዊ የተደረጉ የግብርና ቴክኖሎጂና የምርጥ ዘር አቅርቦቶች የአርሶ አደሩን ውጤታማነት እያሳደጉ መምጣታቸውን ምሁራን ገለጹ። መንግስት የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ ግብርናውን ከማዘመን ባለፈ ወቅትን ጠብቆ ብቻ ከማምረት ልምድ ለማውጣት የበጋ መስኖ ስንዴ ልማትን ተግባራዊ አድርጓል። ይህም የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ተረጂነትን ከማስቀረት ባለፈ የስንዴ ምርትን ወደ ውጭ በመላክ በኩል ከፍተኛ አስተዋጾ እያደረገ ይገኛል። ኢዜአ በመንግስት የግብርና ልማት እቅዶች ትግበራና ውጤታማነት ላይ ከዘርፉ ባለሙያዎችና ተመራማሪዎች ጋር ቆይታ አድርጓል። ሞያዊ ማብራሪያ ከሰጡ የዘርፉ ባለሙያዎች መካከል የብሔራዊ የስንዴ ምርምር ፕሮግራም አስተባባሪና የቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል ተመራማሪ ነጋሽ ገለታ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ የግብርና ልማት ትግበራ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን የመጠቀምና ወቅትን ጠብቆ ከማምረት ልምድ ለመውጣት የሚያስችል ነው። የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር የውኃ አማራጮችን ጥቅም ላይ በማዋል አርሶ አደሩ ዝናብን ብቻ ከመጠበቅ ወጥቶ የመስኖ ልማትን በስፋት በመጠቀም ምርታማነትና ተጠቃሚነቱን እያሳደገ መምጣቱንም ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት የግብርና ልማቱን ውጤታማ እንዲሆን የአፈር ለምነትን ለማሳደግና እርጥበትን ተጠቅሞ ለማልማት የተደረጉ ጥረቶች ስኬት ማስገኘታቸውንም አንስተዋል። በክልሉ ምርጥ ዘሮችን ከመጠቀም በተጨማሪ የኩታገጠም እርሻን ማስፋፋት የአርሶ አደሩን ምርታማነት ማሳደጉን የገለጹት ደግሞ የኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ የባሌ ቅርንጫፍ የአግሮኖሚ ከፍተኛ ባለሙያ አቶ ደሳለኝ ደጀኔ ናቸው። ለዚህም ኢንተርፕራይዙ የስንዴ፣ የገብስና የባቄላ ምርጥ ዘሮችን ለአርሶ አደሩ ከማቅረብ ባለፈ በኩታገጠም አሰራር እና በሰብል እንክብካቤ ላይ ሙያዊ ድጋፍ ማድረጉን አንስተዋል። በምርጥ ዘር አቅርቦቱ በሽታንና ድርቅን የሚቋቋሙ ሰብሎችን ለአርሶ አደሩ በማቅረብ የኢኮኖሚ አቅማቸውን ለማሳደግ የድርሻውን እየተወጣ መሆኑንም አስረድተዋል። በተለይም ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የምርጥ ዘር አቅርቦት በበቂ ሁኔታ ተደራሽ በማድረግ ውጤታማነት ለማሳደግ መሰራቱን አመልክተዋል። በመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የስንዴ ምርምር ፕሮጀክት ዋና አስተባባሪና ተመራማሪ ረዳት ፕሮፌሰር ጀማል አብዱልከሪም በበኩላቸው እንደገለጹት፤ ዩኒቨርሲቲው የመስኖ ስንዴን ልማትን ለማሳደግ አርሶ አደሮችን በሥልጠናና በግብዓት እያገዘ ነው። በተለይም ለባሌ፣ ለምሥራቅ ባሌና ለምዕራብ አርሲ ዞን አርሶ አደሮች ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማት የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም እውቀት እንዲያገኙ ስልጠና መሰጠቱን አስረድተዋል። የግብርና ቴክኖሎጂና የምርጥ ዘር አቅርቦቶች ተደራሽ በማድረግ የአርሶ አደሩን ውጤታማነት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ምርታማነትን በማሳደግ ተጠቃሚ እያደረጉ መሆኑንም አስታውቀዋል።
ግብፅ በዓባይ ወንዝ ምንም ዓይነት የውሃ ምንጭ አበርክቶ ሳይኖራት በኢትዮጵያ ላይ የምታቀርበው መሠረተ ቢስ ክስ ተቀባይነት የለውም
Aug 28, 2026 130
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ግብፅ በዓባይ ወንዝ ምንም ዓይነት የውሃ ምንጭ አበርክቶ ሳይኖራት በኢትዮጵያ ላይ የምታቀርበው መሠረተ ቢስ ክስ ፍጹም ተቀባይነት እንደሌለው የውሃ ሀብት ተመራማሪ ያዕቆብ አርሳኖ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያ የተቸራትን የተፈጥሮ ጸጋዎች እንዳትጠቀም የዘመናት ታሪካዊ ጠላት የሆነችው ግብፅ የውስጥ ባንዳዎችን በመቅጠር ጭምር ከልማትና ዕድገቷ ስትጎትታት መቆየቷ የሺህ ዘመናት የአደባባይ ሐቅ ነው። በዚህ ታሪካዊ ሸፍጥ ቁጭት የገባቸው ኢትዮጵያውያንም ከዓድዋ ጀግኖች የተረከቡትን የጀግንነት ወኔ በመላበስ ታላቁን የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በጉባ ተራሮች ግርጌ ዓባይን በማቀብ ብርሃንን ፈንጥቀዋል። ይህም ዓባይ “ግንድ ይዞ ይዞራል” የተባለለትን የዘመናት ተረትም በመቀየር ሕዳሴ ግድብ የሚያመነጨው ብርሃን ከሀገር የተሻገረ ግዙፍ የኤሌክትሪክ ኃይል በመፍጠር ቀጣናዊ የኢኮኖሚ በረከትን ፈጥሯል። በሕዳሴ ግድብ የተፈጠረው ቀጣናዊ የኃይል ትስስርም የኢትዮጵያን በጋራ የማደግ ቀጣናዊና አፍሪካዊ ራዕይን በአደባባይ የገለጠ አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደት ትልም ሆኖ ተመዝግቧል። የውሃ ሃብት ተመራማሪው ያዕቆብ አርሳኖ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ግብፅ በዓባይ ወንዝ ላይ የምታራምደው የሺህ ዘመናት ወንዙን በብቸኝነት የመጠቀም ግትር አቋም ከራስ ወዳድነት የሚመነጭ ስሁት ትርክት ነው። የሕዳሴ ግድብም የታችኞቹ ተፋሰስ ሀገራትን የደለል ክምችት፣ የጎርፍና የድርቅ አደጋ በመቀነስ እንዲሁም የሀገር ውስጥና ቀጣናዊ የኃይል አቅርቦት ትስስርን በማጠናከር ዘርፈ ብዙ በረከትእያስገኘ ነው ብለዋል። ግብፅ የዓባይን በብቸኝነት የመጠቀም ስግብግብ ፍላጎቷ የሺህ ዘመናት ትርክት መሆኑን አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅትም የግብፅ የፖለቲካ ልሂቃን በቅኝ ግዛት ዘመን ስምምነቶች በመቸንከር ዓባይን በብቸኝነት የመጠቀም ፍላጎትና ሕዳሴ ግድብ ላይ ስሁት ትርክታቸውን በመንዛት ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ኢትዮጵያም ሕዝቦቿን በማስተባበር በዓለም አቀፍ ሕግና መርህ በሳይንሳዊ መንገድ ሕዳሴ ግድብን በመገንባት ፍትሐዊ የድንበር ተሻጋሪ የውኃ ሀብት ተጠቃሚነትን በተግባር ማስመስከሯን አስረድተዋል። ግብፅ ለዓባይ ወንዝ የውኃ ምንጭ ምንም ዓይነት አበርክቶ የላትም ያሉት ተመራማሪው፤ ለሺህ ዘመናት ለብቻየ ልጠቀም የሚለው እሳቤም ኢ-ፍትሐዊ ከመሆኑም ባሻገር መሠረተ ቢስ ፍላጎት ነው ብለዋል። የተፋሰሱን ሀገራት የዓባይ ወንዝ የጋራ ተጠቃሚነት ድርድርና ስምምነቶች በማስተጓጎልም የተሳሳተ አማራጭን እየተከተለች እንደሚገኝ ተናግረዋል። ኢትዮጵያም እስካሁን የውኃ ሀብቶቿን የታችኞቹን የተፋሰስ ሀገራትና ጎረቤቶቿን በማይጎዳ መንገድ ማልማቷን አጠናክራ መቀጠል እንዳለባት አስገንዝበዋል። ግብፅ በሕዳሴ ግድብና በዓባይ ወንዝ ላይ የምታስተጋባው የተሳሳተ መረጃም መሠረተ ቢስ ክስና ማረጋገጫ የሌለው የሺህ ዘመናት ስሁት ትርክት ውጤት መሆኑን አብራርተዋል። ሕዳሴ ግድብና ሌሎች የኃይል ማመንጫ ግድቦች የኢትዮጵያን የውኃ ልማት ዕውቀት፣ ልምድና ተሞክሮ ወደ ላቀ ደረጃ አሸጋግሯል ብለዋል። በቀጣይም በዓለም አቀፍ ሕግና መርህ በመመስረት በዓባይና ሌሎች የውኃ ሀብቶች ላይ ሁለንተናዊ ዕድገትና ብልፅግናን የሚያረጋግጥ የልማት ሥራን ማስቀጠል እንዳለባት ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ለውጭ ሀገራት ከቀረበው የኃይል ሽያጭ 475 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ገቢ አግኝታለች-ኢንጂነር አሸብር ባልቻ
Aug 28, 2026 178
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22 /2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ለውጭ ሀገራት ከቀረበው የኃይል ሽያጭ 475 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ አስታወቁ። ኢንጂነር አሸብር ባልቻ፤ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2019 የትኩረት አቅጣጫዎችን በማስመልከት ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም፤ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ካለፈው በጀት ዓመት በ23 በመቶ ዕድገት በማስመዝገብ የማመንጨት አቅሙ 9 ሺህ 730 ሜጋ ዋት መድረሱን አስታውቀዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ የ124 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ገቢ በማስገኘት የ39 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማስመዝገብ እንደቻለ አስታውቀዋል። የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት የተሳካው አጠቃላይ የእቅዱ 101 ነጥብ 83 ከመቶ አፈጻጸም በተቋሙ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተመዘገበ የትርፍ አፈጻጸም ስኬት መሆኑን አብራርተዋል። ለውጭ ሀገራት ከቀረበው የኃይል ሽያጭም 475 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱን ገልጸው፤ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸርም የ25 በመቶ ብልጫ አለው ብለዋል። በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ ከተመረተው የኤሌክትሪክ ኃይልም የውኃ ማመንጫዎች 97 በመቶ ድርሻ መያዙን ገልጸዋል። በቀጣይም የገናሌ ዳዋ 6 የውኃ ኃይል ማመንጫ፣ የአይሻ 2ኛ የንፋስ ኃይል ማመንጫና በሀገር ውስጥ ፋይናንስ የሚገነባ የ100 ሜጋ ዋት የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶችን ለማስጀመር እቅድ መያዙን አስታውቀዋል። በተጨማሪም የአይሻ ንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ 40 ሜጋ ዋት ኃይል ያመነጫል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል።
በኦሮሚያ ክልል የቱሪስት ፍሰትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት የዘርፉ ገቢ እንዲጨምር አስችሏል
Aug 28, 2026 100
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የቱሪስቶችን ፍሰት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት የዘርፉን የገቢ ምንጭነት እያሳደጉት መምጣታቸውን የክልሉ ደንና የዱር እንስሳት ቢሮ አስታወቀ። የኦሮሚያ ደንና የዱር እንስሳት ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አራርሳ ረጋሳ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የደን ሃብትን በማልማት ለአካባቢ ጥበቃ ትልቅ ትኩረት ከመስጠት ባሻገር የቱሪዝም መስህብና የሀብት ምንጭ ማድረግ ስለመቻሉ አንስተዋል። በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ የደን ሽፋን በማደጉ የዱር እንስሳት ደህንነት እንዲጠበቅና ሸሽተው የነበሩም እንዲመለሱና ይበልጥ እንዲበራከቱ እድል ተፈጥሯል ብለዋል። በዚህም የዱር እንስሳትና ብርቅዬ አእዋፋት ጭምር ሁነኛ የጎብኝዎች መስህብ እየሆኑ በመምጣታቸው አበረታች ገቢ እየተገኘ መሆኑን ገልጸዋል። የዘርፉ ልማት የስነ-ምህዳር መታደስን ከመፍጠሩ በላይ፣ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶችን ትኩረት መሳብ ያስቻለ ስለመሆኑም አስረድተዋል። በክልሉ የሚገኙ ብሔራዊ ፓርኮችን ተፈጥሮአዊ ሀብት ከመጠበቅ ጎን ለጎን ሕጋዊ የአደን ስፍራዎችን በመለየት የገቢ ምንጭ እንዲሆኑ ማድረግ ተችሏል ነው ያሉት። በእርጅና ላይ የሚገኙና ጉዳት የደረሰባቸውን የዱር እንስሳት በመለየትም እንክብካቤ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልጸዋል።