ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በምስራቅ ሸዋ ዞን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የግብርና ምርቶች ኤክስፖርትን ለማሳደግ የሚደረጉ ጥረቶች ተጠናክረው ቀጥለዋል
Aug 11, 2026 256
አዳማ፤ ነሐሴ 5/2018(ኢዜአ) ፡-በምስራቅ ሸዋ ዞን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የግብርና ምርቶች ኤክስፖርትን ለማሳደግ የሚደረጉ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባቡ ዋቆ ገለፁ። የምስራቅ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባቡ ዋቆን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ የዞኑ አመራሮች በቦሰት ወረዳ በኩታገጠም የለማውን የቦሎቄና በቆሎ ሰብል ያለበትንና የእንክብካቤ ሂደትን ጎብኝተዋል።   አቶ አባቡ ዋቆ በወቅቱ እንዳሉት፤ በዞኑ በምግብ ራስን ለመቻልና የኤክስፖርት ምርቶችን ለማሳደግ የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት እየሰራን ነው። በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን ከ580 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዋና ዋና ሰብሎች በቴክኖሎጂ በታገዘ አሰራር በዘር መሸፈኑን ለአብነት አንስተዋል። በተለይም በዘንድሮው ዓመት የአርሶአደሩን ምርትና ምርታማነት ለመጨመር የሜካናይዜሽን አገልግሎቱን በስፋት ለአርሶአደሩ ተደራሽ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። አጠቃላይ በሰብል ከተሸፈነው የዞኑ መሬት ውስጥ ከ91 በመቶ በላይ በሜካናይዜሽን በመደገፍና ቴክኖሎጂን በመጠቀም በኩታገጠም የለማ መሆኑንም አንስተዋል። በዋናነት ከውጭ የሚገቡ የግብርና ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ የኤክስፖርት ምርቶችን ለማሳደግ የተቀመጠውን ሀገራዊ ግብ እውን ለማድረግ በሚደረገው ሂደት ውስጥ የዞኑ ድርሻ የላቀ ነው ብለዋል። ለዚህም አርሶአደሩ ገበያ ተኮር ምርቶችን በተለይም ቦሎቄ፣ ማሾ፣ ሽንብራ እንዲሁም ስንዴን በስፋት በኩታገጠም እያለማ ይገኛል ብለዋል። በየደረጃው የሚገኙ የዞኑ አመራሮች በየዕለቱ በአርሶአደሩ ማሳ በመገኘት ቡቃያው የለበትን ሁኔታ በመመልከት በእንክብካቤው በተለይም በአረምና የሰብል በሽታን በመከላከል ላይ የተሟላ እገዛ ማድረግ የጉብኝቱ ዓላማ መሆኑንም ተናግረዋል። የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ መስፍን ተሾመ በበኩላቸው በዞኑ ከመደበኛው የሰብል ልማት በተጓዳኝ የግብርና ኤክስፖርት ምርቶች ላይ እየሰራን ነው ብለዋል። በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ88ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቦሎቄ በኩታገጠም መልማቱን ለአብነት አንስተዋል።   ከዚህም ከሁለት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል ያሉት አቶ መስፍን፤ ከሚገኘው ምርትም 900 ሺህ ኩንታል ያህሉ ወደ ውጭ ይላካል ብለዋል። የኤክስፖርት ቦሎቄ ልማቱን አርሶአደሮቹ ከባለሀብቶች ጋር በኮንትራት እርሻ ውል እያለሙ መሆኑንም ገልጸዋል።
በክልሉ በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ማስፋፋት ሥራዎች ውጤታማነትን እያሳደጉ ነው
Aug 11, 2026 158
ቡታጅራ፤ ነሐሴ 5/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ማስፋፋት ሥራዎች የኢንዱስትሪውን ውጤታማነት ይበልጥ እያሳደገው መሆኑ ተገለጸ። የክልሉ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ከ312 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ላስመዘገቡ ኢንዱስትሪዎች በቡታጅራ ከተማ ያስገነባቸውን የማምረቻ ሼዶች ዛሬ አስረክቧል።   የኮርፖሬሽኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ናትናኤል ሚሊዮን በዚሁ ወቅት፣ ኮርፖሬሽኑ የአምራች ኢንዱስትሪውን ውጤታማነት ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወነ መሆኑን አንስተዋል። በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶችን ከማበረታታት ባለፈ የመስሪያና የመሸጫ ሼዶችን ጨምሮ የመሰረተ ልማት ተደራሽነትን በማስፋፋት ለሥራቸው ምቹ ሁኔታ እየፈጠረም ይገኛል። በዚህም በዘርፉ የተሰማሩ የግል ባለሀብቱን እና ሥራ አጥ ዜጎችን ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉን ገልጸው፣ ከውጭ የሚገባ ምርትን በሀገር ውስጥ በመተካትም ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬን ለማዳን ተችሏል ብለዋል። በዛሬው እለትም ከ312 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ላስመዘገቡ 7 አምራች ኢንዱስትሪዎች ስምንት ሼዶች የተላላፉ መሆኑን ገልጸው፣ ኢንዱስትሪዎቹ ከ 387 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥሩ ተናግረዋል። አቶ ናትናኤል እንዳሉት፣ ኮርፖሬሽኑ አነስተኛና መካከለኛ አምራች ኢንዱስትሪዎችን በተለያየ መንገድ በመደገፍ በዘርፉ እየተመዘገበ ያለውን ተጨባጭ ውጤት ለማስቀጠል የጀመረውን ሥራ ያጠናክራል። ዛሬ የማምረቻ ሼድ ከተላለፈላቸው ኢንዱስትሪዎች መካከል በዱራሜ ከተማ የከምባታ ቡና ማቀነባበሪያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ምትኩ ሰልፊሶ በሰጡት አስተያየት ኢንዱስትሪው 150 ሚሊዮን ብር ካፒታል በማስመዝገብ መቋቋሙን ተናግረዋል።   በአሁኑ ወቅትም ከ150 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜአዊ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር ጠቁመው፣ በኮርፖሬሽኑ የተመቻቸላቸው የማምረቻ ሼድ ለስራቸው ውጤታማነት አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። ሌላኛው በሀደሮ ከተማ በዝንጅብል ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ዘርፍ የተሰማራው የሱዳስ ግሩፕ ሥራ አስኪያጅ አቶ አስፋው አበበ በበኩላቸው ኢንዱስትሪው በ70 ሚሊዮን ብር የመነሻ ካፒታል ወደሥራ መግባቱን ተናግረዋል።   ኢንዱስትሪው ለ100 ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። የማምረቻ ሼዶችን ለአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለማስተላለፍ በተዘጋጀው መርሐ ግብር ላይ የክልል ከፍተኛ አመራሮችና በዘርፉ የተሰማሩ ባለሀብቶች ተሳትፈዋል።    
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በሥራ ዕድል ፈጠራ በተከናወኑ ሥራዎች ውጤት ተገኝቷል
Aug 11, 2026 197
ሆሳዕና፤ ነሀሴ 5/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ዜጎችን በሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ በተከናወኑ ሥራዎች ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ አስታወቀ።   የቢሮው ሀላፊ አቶ ሙስጠፋ ኢሳ ለኢዜአ እንደገለጹት በግብርና፣ በአገልግሎት፣ በእንጨትና ብረታብረት እንዲሁም በሌሎች መስኮች የሥራ ዕድል በመፍጠር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተጀመሩ ተግባራት ውጤት ተመዝግቧል።   ቢሮው በ2018 በጀት ዓመት በግብርና፣ በአገልግሎትና በኢንዱስትሪ ዘርፍ ለ400 ሺህ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል ለመፍጠር አቅዶ ከ379 ሺህ 430 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉን ተናግረዋል። የሥራ ዕድል ፈጠራውን ውጤታማ ለማድረግም በበጀት ዓመቱ ከ925 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር በላይ ብደር መመቻቸቱን፣ 8 ሺህ 420 ሄክታር መሬት መቅረቡን እና 689 አዳዲስና ነባር ሼዶች ለኢንተርፕራይዞች እንዲተላለፉ መደረጉን ተናግረዋል።   በበጀት ዓመቱ የሥራ እድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል በጉራጌ ዞን እምድብር ከተማ ነዋሪ ወጣት ዳዊት ትዛዙ እንዳለው ከመንግስት ባገኘው የገንዘብ ብድር በቅመማ ቅመም፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሥራ መሰማራቱን ጠቁሟል። በአራት ሄክታር መሬት ላይ እያለማ ያለውን ቲማቲም ሽንኩርትና ሌሎች የጓሮ አትክልቶችን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆን መጀመሩንም ተናግሯል።   በአሁኑ ወቅትም ከራሱ ባለፈ ለሌሎች ሥራ አጥ ወገኖች ጊዜያዊ ሥራ ዕድል በመፍጠር ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም ገልጿል። በመንግስት ካገኘው የገንዘብ ብድር በተጨማሪ በተሰማራበት የእርሻ ሥራ ውጤታማ እንዲሆን በግብርና ባለሙያዎች ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግለትም ተናግሯል። ሌላው በሆሳዕና ከተማ ነዋሪ ወጣት ዳንኤል አሰፋ በበኩሉ በከተማው በሚገኘው ታዴ የእንስሳት መኖ ማቀነባበሪያ ኢንተርፕራይዝ ቋሚ የሥራ ዕድል እንደተፈጠረለት ገልጿል።   በዚህም በሚያገኘው ገቢ እራሱን ከማስተዳደሩ በተጨማሪ ነገ የራሱን ሥራ በመፍጠር ሕይወቱን የተሻለ ደረጃ ላይ ለማድረስ ራዕይ እንዲሰንቅ ማድረጉን ተናግሯል።  
በሙስናና ሕገ ወጥ ድርጊት የተሰማሩ አካላትን ተጠያቂ የማድረግ ርምጃ ቀጣይነት ሊኖረው ይገባል
Aug 11, 2026 242
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 5/2018 (ኢዜአ)፦የመንግሥት በሙስናና ሕገ ወጥ ድርጊት የተሰማሩ አካላትን በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ርምጃ ቀጣይነት ሊኖረው እንደሚገባ ኢዜአ ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ ህገወጥነትን በመከላከልና በማጋለጥ በኩል ህብረተሰቡ ተሳትፎውን ማጠናከር እንዳለበትም ጠቁመዋል። መንግሥት በተደራጀ ሙስናና ሕገወጥ ድርጊቶች የተሰማሩ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር በማዋል የሕግ የበላይነትን እያረጋገጠ እንደሚገኝ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት በሰጠው መግለጫ አሳውቋል፡፡ ኢትዮጵያን የአፍሪካ የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ የተቀመጠውን ራዕይ ለማሳካት ከልማት ሥራዎች ባሻገር የሕግ የበላይነትን ማስፈን ቀዳሚ ተግባሩ አድርጎ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ የመንግሥትን ሕግ የማስከበር ርምጃ በተመለከተ ኢዜአ ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ነዋሪዎች እንዳሉት፤ የህዝብን ሀብት ከምዝብራና ብክነት መጠበቅ የመንግሥት ትኩረት ሊሆን ይገባል፡፡ በቅርቡ መንግሥት በሙስናና ሕገ ወጥ ድርጊቶች ላይ የተሳተፉ አካላትን በቁጥጥር ስር በማዋል ተጠያቂነትን ለማስፈን የወሰደው እርምጃ ተገቢና ቀጣይነት ሊኖረው የሚገባ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከአስተያየት ሰጭዎች መካከል ሄኖክ ተስፋዬ፤ ርምጃዎቹ የሕግ የበላይነትን በማስፈን የመንግስትና የህዝብን ሀብት ከምዝበራ ማዳን ነው ብለዋል፡፡ በብልሹ አሰራርና ባልተገቡ አሰራሮች ላይ እየተወሰደ ያለው ርምጃ የመንግሥትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ እና በዜጎች ዘንድ ደግሞ መተማመንን የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል፡፡   ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ትዕግስት ገብረየስ፤ መንግሥት ተጠያቂነትን ለማስፈን የሚወስደው ርምጃ እስከታች ባለው የመንግሥት መዋቅር ገቢራዊ መደረግ አለበት ብለዋል፡፡ መንግሥት ተጠያቂነትን ለማስፈን የጀመረው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን በማንሳት፤ ሂደቱ ቀጣይነት ሊኖረው እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ወጣት ቴዲ ዑለማ በበኩሉ፤ መንግሥት የህግ የበላይነትን ለማስፈን የተግባር ቁርጠኛ መሆኑን ያሳየ ርምጃ መሆኑን ተናግሯል፡፡   ሌላው አስተያየት ሰጪ አቢቲ ረጋሳ ሙስናና ብልሹ አሰራር የዕድገት ማነቆ መሆኑን በመግለጽ፤ ርምጃው አስተማሪና ትምህርት ሰጭ ነው ብለዋል፡፡   ማንም ሳይለፋና ሳይሰራ መበልጸግ የለበትም፤ ሙሰኞችን ለህግ ማቅረብ ተጠናክሮ መቀጠል ህዝቡም መተባበር አለበት ያሉት ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ በለጡ ዘላለም ናቸው፡፡      
በጉጂ ዞን ለመኸር አዝመራ ከተዘጋጀው መሬት ከ106 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Aug 11, 2026 179
አዶላ፣ ነሐሴ 5/2018(ኢዜአ) ፡-በጉጂ ዞን ለመኸር አዝመራ ከተዘጋጀው መሬት እስካሁን ከ106 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በተለያዩ የሰብል ምርጥ ዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በኦሮሚያ ክልል የጉጂ ዞን በቆላማ፣ በደጋ እና በወይና ደጋ አየር ንብረቶች የተከፋፈለ በመሆኑ የተለያዩ የሰብል ዓይነቶችን ለማምረት አመቺ ተፈጥሮ አለው። በዞኑ ከነሐሴ እስከ መስከረም አጋማሽ የዝናብና የዘር፣ እንዲሁም ከታኅሣሥ እስከ ጥር መጨረሻ የምርት ስብሰባ ወቅት ሲሆን፤ በመኽር ወቅት በብዛት ከሚመረቱ ሰብሎች መካከል በቆሎ፣ ስንዴ፣ ገብስ፣ ጤፍ፣ ቦሎቄ እና ዘይት ነክ ሰብሎች ይጠቀሳሉ።   በዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት የሰብል ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ መንግሥቱ ሂርባዬ እንደገለጹት፤ ለተያዘው የመኸር አዝመራ 498 ሺሕ 778 ሄክታር መሬት በተለያዩ ምርጥ የሰብል ዘር በማልማት ከ13 ሚሊዮን 200 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዷል። በተያዘው የመኽር እርሻ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተሻሻሉ የግብርና አሠራሮችን መተግበርና ግብዓቶችን በአግባቡ መጠቀም ትኩረት ተሰጥቶታል ብለዋል። በዚህም መሠረት የሜካናይዜሽን እርሻን ማስፋፋት፣ በኩታገጠም የመሬት ዝግጅትና በመስመር የመዝራት ዘዴዎችን በመጠቀም ረገድ ሰፊ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በመኽር ልማቱ እስከ አሁን በተደረገው እንቅስቃሴ፤ 119 ሺሕ 216 አርሶ አደሮችን በማሳተፍ 106 ሺሕ 159 ሄክታር መሬት በኩታ ገጠም አሰራር በተለያዩ ምርጥ የሰብል ዘሮች መሸፈኑን አስታውቀዋል። በዞኑ በመኽር አዝመራው ከሚለሙት የተለያዩ የሰብል ዓይነቶች መካከል፤ በዋናነት እንደ ጤፍ፣ ስንዴ፣ ገብስ፣ ባቄላ እና ቦለቄ ያሉ የእህልና የጥራጥሬ ሰብሎች ይጠቀሳሉ ብለዋል። ከግብዓት አቅርቦት አንጻርም በዞኑ ለሚገኙ ሁሉም ወረዳዎች 12 ሺሕ 429 ኩንታል ምርጥ ዘር እና 71 ሺሕ 600 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ማቅረብ መቻሉን አስታውቀዋል። በእርሻው ተሳታፊ ከሆኑት አርሶ አደሮች መካከል በዞኑ የአዶላ ሬዴ ወረዳ የደራርቱ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ኔንቆ ዋሬ፤ ባለፈው የምርት ዘመን የተሻሻሉ የግብርና አሠራሮችን በመተግበር ካለሙት የእርሻ መሬት የተሻለ ምርት መሰብሰባቸውን ያስታውሳሉ። ካለፈው ዓመት ያገኙትን በጎ ተሞክሮ መሠረት በማድረግ፤ በዘንድሮው የመኽር እርሻ በኩታ ገጠም ለማልማት ካዘጋጁት ማሳ ከፍተኛ ምርት ለማግኘት አልመው በትጋት እየሠሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል።   የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ማቴዎስ አዱላ በበኩላቸው፤ ለምርት ዘመኑ የሚያስፈልጉ የግብርና ግብዓቶች በወቅቱና በበቂ ሁኔታ እንደቀረበላቸው አንስተው፣ የታቀደውን ምርትና ምርታማነት ለማሳካት የግብርና ባለሙያዎች በቅርበት ዕገዛ እያደረጉላቸው መሆኑን አክለዋል። የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴ የሰብል ልማቱን ውጤታማ ለማድረግ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የጠቆሙት አርሶ አደሩ፤ አሠራሩ አላስፈላጊ ወጪንና ጉልበትንም የሚቀንስ ነው ብለዋል።  
የአርባ ምንጭ ኮንፈረንስ ሪዞርት የቱሪዝም ዘርፉን የሚያነቃቃና ለከተማዋም ተጨማሪ ድምቀት ነው
Aug 11, 2026 251
አርባ ምንጭ፤ ነሐሴ 5/2018 (ኢዜአ)፡-በገበታ ለትውልድ መርሐግብር የተገነባው የአርባ ምንጭ ኮንፈረንስ ሪዞርት የቱሪዝም ዘርፉን የሚያነቃቃና ለከተማዋም ተጨማሪ ድምቀት መሆኑ ተገለጸ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢኒሼቲቭ የተገነባውና የገበታ ለትውልድ ፕሮጀክት አካል የሆነው አርባ ምንጭ ኮንፈረንስ ሪዞርት በቅርቡ መመረቁ ይታወቃል። ኢዜአ ያነጋጋራቸው የአርባ ምንጭ ከተማ ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ አቶ ደስታ ደምበላ እንደገለጹት ሪዞርቱ ለአካባቢው ብሎም ለሀገር ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያለው ግዙፍ የልማት ፕሮጀክት ነው።   ሪዞርቱ የገበታ ለትውልድ ፕሮጀክት አካል መሆኑንም ጠቅሰው፣ የቱሪዝምና የአገልግሎት ዘርፉን ከማነቃቃት ባለፈ ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር አስተዋጾ እንደሚኖረው ተናግረዋል። ሪዞርቱ የተገነባበት ቦታ ለቱሪዝም ምቹ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ደስታ፣ በተለይ በዓባያ ሐይቅ ላይ የተገነባው ተንሳፋፊ ሬስቶራንት የተለየ በመሆኑ የጎብኚዎችን ቀልብ ይስባል ብለዋል ። እንደሃላፊው ገለጻ የአካባቢውን የቱሪዝም ፀጋዎች ይበልጥ እንዲታወቁ በማድረግ በኩልም ፋይዳው የጎላ ሲሆን ሀገራዊ ጠቀሜታም ከፍተኛ ነው ብለዋል። የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪው አፈወርቅ አለማየሁ በበኩላቸው እንዳሉት፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በገበታ ለሀገርና ገበታ ለትውልድ ያስገነቧቸው ፕሮጀክቶች የሀገርን ገጽታ በመሰረታዊነት የቀየሩ ናቸው።   ሪዞርቱ በአርባ ምንጭና አካባቢው የሚገኘውን የሸማ ጥበብ፣ የባህል፣ የምግብና የአልባሳት ሥራዎችን ለማስተዋወቅና ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ ምቹ ዕድል ይፈጥራል ሲሉም አክለዋል። በግንባታው ሂደት ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን አስታውሰው፣ በቀጣይም ለዜጎች በቋሚና በጊዜያዊነት ተጨማሪ የሥራ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ሙና ዮሐንስ ሪዞርቱ የከተማዋን ውበት አጉልቶ የሚያወጣ ተጨማሪ ፀጋ ነው ሲሉ ገልጸዋል።   ወጣት ታምራት በርገኔ በበኩሉ ሪዞርቱ የአርባ ምንጭ ከተማን ገጽታ ይበልጥ ከማድመቅ ባለፈ ቱሪስትን በመሳብ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ገልፆ፣ ይህም ለከተማዋና ለሀገር እድገት የሚኖረው አበርክቶ የጎላ ነው ብሏል።   አስተያየት ሰጪዎቹ በአርባ ምንጭና አካባቢው ሰፊ የቱሪዝም አቅም በመኖሩ ሪዞርቱ ከሀገር ውስጥና ከውጭ ወደ ከተማዋ ለሚመጡ ቱሪስቶችና እንግዶች ምቹ ማረፊያ እንደሚሆንም ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ የተመረቀው የአርባ ምንጭ ኮንፈረንስ ሪዞርት የቱሪዝም መዳረሻዎችን ከማስፋፋት ባለፈ የሀገር የኢኮኖሚ አቅምን ከፍ ለማድረግ ሚናው የጎላ ነው። ሪዞርቱ ከ1ሺህ 300 በላይ ሰዎችን የሚያስተናግድ የስብሰባ አዳራሽና በሐይቅ ላይ የተገነባ ልዩ ተንሳፋፊ ሬስቶራንትን ያካተተ እንደሆነም በወቅቱ ተመላክቷል። ጠቅላይ ሚኒስትሩም "ሪዞርቱ የኮንፈረንስ ቱሪዝምን በማስፋፋት ኢትዮጵያን የዓለም አቀፍ መድረኮች ማዕከል የማድረግ ራዕያችንን ያጠናክራል፤ ለአካባቢውም ማህበረሰብ ሰፊ የሥራ ዕድል ፈጥሯል" ሲሉ በወቅቱ መግለጻቸው የሚታወስ ነው።    
በሐረሪ ክልል ለኢንዱስትሪው ዘርፍ የተደረጉ ድጋፎች ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል
Aug 11, 2026 443
ሐረር ፤ነሐሴ 5/2018 (ኢዜአ) ፡-በሐረሪ ክልል የኢንዱስትሪውን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ለማጉላት የተደረጉ ድጋፎች ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገባቸውን የክልሉ ኢንተርፕራይዝ እና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ እስማኤል ዩሱፍ ገለፁ። በክልሉ ለኢንዱስትሪ ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት የሥራ እድል ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ወጣቶች ተናግረዋል።   የክልሉ ኢንተርፕራይዝ እና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ እስማኤል ዩሱፍ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንዳሉት፤ በክልሉ ለኢንዱስትሪ ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት 231 አነስተኛ፣ መካከለኛና ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ እንዲገቡ አድርጓል። የኢንዱስትሪ ዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግም የመሠረተ ልማት አቅርቦት፣ ድጋፍና ክትትል መጠናከሩን ተናግረዋል።   ይህም የኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም በማሳደግ፣ ከ49 ሺህ ቶን በላይ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በመተካት 60 ሚሊዮን ዶላር የሚጠጋ የውጭ ምንዛሬ ማዳን መቻሉን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ማደግ ለዜጎች የሥራ ዕድል እንዲፈጠር ማስቻሉንም ተናግረዋል። በቀጣይም አዳዲስ ኢንቨስትመንቶችን በተለይ የኮንስትራክሽን፣ የምግብና መጠጥ፣ የቆዳና የቆዳ ውጤቶችና ሌሎች ዘርፎችን የማስፋፋትና የማዘመን ሥራ በትኩረት ይከናወናል ብለዋል።   በክልሉ በተደረገላቸው ድጋፍ ውጤታማ ከሆኑ ኢንዱስትሪዎች መካከል የታቲ የከረጢትና ጫማ ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ አቶ ዑመር መሐመድ እንዳሉት፤ ፋብሪካው ፌስታልን ከማምረት ወጥቶ ተኪ የሆኑ የከረጢትና የጫማ ምርቶችን ማምረት መጀመሩን ተናግረዋል። ይህም የማምረት አቅሙን በማሳደግ በገበያ ተወዳዳሪ ከመሆን አልፎ፣ ለአገር እድገት ያለውን አበርክቶ በማሳደግ ለዜጎች የሥራ እድል መፍጠሩን ጠቁመዋል።   በክልሉ የአምራች ኢንዱስትሪ መስፋፋትን ተከትሎ በተፈጠረለት የሥራ እድል ተጠቃሚ በመሆኑ ራሱንና ቤተሰቡን ከመደገፍ ባለፈ የቴክኖሎጂ ክህሎቱን እያዳበረ መሆኑን የተናገረው ደግሞ ወጣት መሐመድ ዙቤር ነው። በክልሉ ኢንዱስትሪ ዞን በአልባሳት ማምረት ላይ በተሰማሩ ኢንዱስትሪዎች የሥራ እድል ከተፈጠረላቸው መካከል ጽዮን ሻውል በበኩሏ፤ የተገኘው የሥራ እድል ቤተሰቧን ለማስተዳደር እንዳገዛት ተናግራለች።  
የወዳጅነት ፓርክ ባለፉት አራት ዓመታት ብቻ ወደ አንድ ቢሊዮን ብር ገደማ ገቢ አስገኝቷል
Aug 11, 2026 271
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 4 /2018(ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ መሐል የሚገኘው የወዳጅነት ፓርክ ባለፉት አራት ዓመታት ብቻ ወደ አንድ ቢሊዮን ብር ገደማ ገቢ አስገኝቷል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት የወዳጅነት ፓርክ ባለፉት ስምንት ዓመታት በመደመር መንግሥት ከተገነቡት የመጀመሪያዎቹ ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው የሕዝብ መገልገያ ቦታዎች አንዱ ነው ብለዋል። በዚህም ይህ ፓርክ ባለፉት አራት ዓመታት ብቻ ወደ አንድ ቢሊዮን ብር ገደማ ገቢ ያስገኘ ሲሆን፣ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሥራ ዕድሎችንና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ፈጥሯል ነው ያሉት። ከሁሉም በላይ ደግሞ ከተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች የተውጣጡ ዜጎችና ጎብኝዎች የሚገናኙበት ሥፍራ መሆን ችሏል።   ከቤተሰቦችና ሕፃናት፣ከስፖርት ቡድኖችና ከሠርግ ተካፋዮች ጀምሮ እስከ ዲጂታል ይዘት ፈጣሪዎች፣ እንዲሁም የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር ጎብኚዎች በቦታው ይገኙበታል። የወዳጅነት ፓርክ ከኢኮኖሚያዊ እሴቱ ባሻገር ለጤና፣ ለአካል ብቃት፣ ለመዝናኛና ለሕብረተሰብ ትስስር ትልቅ አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። ይህም በጥሩ ሁኔታ የታቀዱ የሕዝብ መገልገያ ሥፍራዎች ለአዲስ አበባ ከተማ አጠቃላይ የከተማነት ዕድገት አስተዋጽኦ እያበረከቱ ሰዎችን እንዴት ማገናኘት እንደሚችሉ ማረጋገጫ ነው ያሉት።   ይህ ፓርክ በከተማዋ እንዲሁም በሌሎች ከተሞች ውስጥ እየተገነቡ ላሉ ተመሳሳይ የሕዝብ መገልገያ ሥፍራዎች ቀዳሚ ማሳያ እንደሆነም ገልጸዋል። እነዚህ አዳዲስ ቦታዎች እሴት የሚፈጥሩ፣ ዕድሎችን የሚያመቻቹ እና ከሁሉም በላይ ደግሞ የኢትዮጵያውያንን ባለቤትነትን የሚያረጋግጡ ማዕከላት መሆናቸውን ነው የገለጹት።
በጎንደር ከተማ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለሥርዓተ ምግብ መሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
Aug 11, 2026 217
ጎንደር፤ ነሐሴ5 /2018 (ኢዜአ) ፡-በጎንደር ከተማ የተተገበረው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለሥርዓተ ምግብ መሻሻልና ለሥራ እድል ፈጠራ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያ ኃላፊው አቶ መላኩ ደምሌ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በጎንደር ከተማ የተተገበረው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለሥርዓተ ምግብ መሻሻልና ለሥራ እድል ፈጠራ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው።   በከተማው የሚገኙ ቀበሌዎችን በሥጋ፣ በወተት፣ በማር፣ በዶሮና በሌሎች የልማት ዘርፎች በኩታ ገጠም በማደራጀት ወደ ሥራ መገባቱን አውስተዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ108 ሚሊዮን ሊትር በላይ የወተትና እስከ 65 ሚሊዮን የሚደርስ የእንቁላል ምርት ማምረት መቻሉን ገልጸዋል። የእንቁላል ምርቱም የአካባቢውን የገበያ ፍላጎት ከመድረስ ባለፈ ወደ ሱዳን ጭምር በመላክ የአምራቾችን ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል። በተለይም የወተት ምርታማነትን ለማሳደግ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የላሞች ዝርያ ማሻሻል በመሰራቱ፣ በቀን ከአንድ ላም በአማካይ የሚገኘውን ወተት 42 ሊትር ማድረስ ተችሏል ብለዋል። በ2018 በጀት ዓመት ለ8 ሺህ 790 ወጣቶች በዘርፉ አዲስ የሥራ እድል መፈጠሩን አስረድተዋል። የከተማዋ ነዋሪ የሆኑት አቶ አያልነው ማሩ እንደገለጹት፤ በዘመናዊ የወተት ከብቶች እርባታ ላይ በመሰማራታቸው ለውጥ ማምጣት ችለዋል። ሥራውን በሦስት ላሞች የጀመሩት አቶ አያልነው፣ አሁን ላይ ከ80 በላይ ላሞች ማድረስ መቻላቸውን ጠቁመው በቀን እስከ 400 ሊትር ወተት በማምረት እያቀረቡ እንደሚገኙ አስረድተዋል። በላም እርባታና ወተት ማምረት ሥራውም እስከ 25 ለሚሆኑ ቋሚና ጊዜያዊ ሰራተኞች የሥራ እድል መፍጠር መቻላቸውን ተናግረዋል።   ሌላኛው የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የእንስሳት ሕክምና መምህር ዶክተር ካሳሁን በሬ በበኩላቸው፤ ከመደበኛ ሥራቸው ጎን ለጎን ከ2009 ዓ.ም ጀምሮ በዶሮ እርባታ ዘርፍ በመሰማራት ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። አሁን ላይ ለ10 ሰዎች በቋሚና በጊዜያዊነት የሥራ እድል መፍጠራቸውን ጠቁመው፣ ወደ ዘርፉ ለሚቀላቀሉ ሌሎች ወጣቶች ነፃ የሙያ ድጋፍ እየሰጡ እንደሚገኙም አስረድተዋል።  
በዘላቂ ሰላምና ልማት ስራዎች ሚናችንን እናጠናክራለን-የመንግስት ሰራተኞች
Aug 10, 2026 746
ገንዳውኃ፣ ነሃሴ 4/2018 (ኢዜአ):- ዘላቂ ሰላምን በማስፈን ልማትን አጠናክሮ ለማስቀጠል በሚከናወኑ ተግባራት ሚናቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በምዕራብ ጎንደር ዞን የገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር የመንግስት ሰራተኞች ገለጹ። የከተማው አስተዳደር ከመንግስት ሠራተኞች ጋር በሰላም፣ ጸጥታ እና በልማት ስራዎች ዙሪያ ምክክር አካሂዷል። በውይይት መድረኩ የተሳተፉ የመንግስት ሰራተኞች በከተማው በሚከናወኑ በዘላቂ ሰላምና ልማት ስራዎች ሚናቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። ከሰራተኞች መካከል አቶ በረከት ገብሬ እንደገለጹት፣ ሰላምን በዘላቂነት ማረጋገጥ ለልማት ስራዎች መፋጠን ወሳኝ ነው ። ሰላምን በዘላቂነት በማረጋገጥ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ዳር ለማድረስ በሚከናወኑ ተግባራት ሚናቸውን እንደሚያጠናክሩ አመልክተዋል ። "የመንግስት ሰራተኛው የህብረተሰቡ ግንባር ቀደም አገልጋይ እንደመሆኑ መጠን፣ የአካባቢውን ሰላም በማስጠበቅ እና የጸጥታ ስጋቶችን ቀድሞ በመከላከል ረገድ አርአያነታችንን ማሳየት አለብን" ብለዋል። ከድጃ ሙሳ በበኩላቸው፣ የህዝቡን የአገልግሎት ፍላጎት በታማኝነትና በጥራት ማሟላት ለሰላም መረጋገጥ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመዋል። "በየመሥሪያ ቤታችን ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት ለዘላቂ ሰላምና ልማት መረጋገጥ ​አበርክቷችንን እናጠናክራለን ብለዋል ።   ​የገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ አቶ አዳነ ሀሰን በበኩላቸው፣ በከተማ አስተዳደሩ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን በፍጥነት ለማጠናቀቅ የሰራተኛው ተነሳሽነት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። ​የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በየደረጃው በመፍታት፣ ሰላምን የሚያጽኑና የአገልግሎት አሰጣጥን የሚያፋጥኑ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።   የምዕራብ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ በወቅቱ እንዳሉት፣ የመንግስት ሰራተኛው የመልካም አስተዳደርና የልማት ስራዎችን ግንባር ቀደም መሪ ሆኖ ሊፈፅም ይገባል። በተለይም ሰላምን በዘላቂነት የማረጋገጥ ስራ የሁሉም መሰረት መሆኑን አመልክተዋል ። ​ሰራተኛው ከህብረተሰቡ ጋር በቅርበት በመስራት የሰላም አምባሳደር ሊሆን እንደሚገባ እና ለአካባቢው ደህንነት መጠበቅ የድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል ።  
የኦዲት ጥራትን ለማሻሻል ባለሙያዎች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ታሳቢ በማድረግ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል
Aug 10, 2026 749
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፦የኦዲት ጥራትን ለማሻሻል ባለሙያዎች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ታሳቢ በማድረግ በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ ገለጸ። የኢትዮጵያ ሒሳብ አያያዝና ኦዲት ቦርድ በኦዲት ጥራት የግምገማ ውጤቶች ዙሪያ ከኦዲት ባለሙያዎችና ባለድርሻ ተቋማት ጋር ተወያይቷል።   የቦርዱ ዋና ዳይሬክተር ውብእሸት ታደለ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኦዲተሮች የሒሳብና የኦዲት ሪፖርቶችን ጥራት ለማረጋገጥ ዓለም አቀፍ የሙያ ደረጃዎችንና የሥነ-ምግባር መርሆዎችን በጥብቅ ክትትል ነጻና ገለልተኛነት ሆነው ሊሰሩ ይገባል። በግምገማው የታዩ የኦዲት ጥራት ክፍተቶችን ለመሙላት የባለሙያዎችን አቅም ማጎልበት፣ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ማስፋፋትና የሙያ ደረጃዎችን ማስጠበቅ አስፈላጊ መሆኑም አስገንዝበዋል። የቦርዱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ አጎናፍር በበኩላቸው፤ ጥራት ያለው የኦዲት ሪፖርት ኢንቨስትመንትን ለመሳብ፣ የታክስ ሥርዓቱን በብቃት ለማስኬድና የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማጠናከር ወሳኝ ሚና እንዳለው ጠቁመዋል።   ኢትዮጵያ ወደ ካፒታል ገበያ እየተሸጋገረች በመሆኑም ዓለም አቀፍ ደረጃን የጠበቀ የኦዲት ሥርዓት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ኦዲተሮች ለሒሳብ አያያዝና ኦዲት ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ መልዕክት አስተላልፈዋል።   የውጭ ኦዲተሮች ማኅበር ፕሬዝዳንት ዳንኤል ጌታነህ፤ የኦዲት ድርጅቶች የሰው ኃይልና የቴክኖሎጂ አቅማቸውን መፈተሽና ክፍተት ያለባቸውን ማጠናከር የኦዲት ጥራትን ለማሻሻል ቁልፍ ነው ብለዋል። የኮከብና መልካሙ ኦዲት አድራጊ ድርጅት ተወካይ ኮከብ ሞገስ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የአካውንቲንግ ትምህርት ከንድፈ ሀሳብ ባሻገር የተግባር ልምምድን ያካተተ እንዲሆን በማድረግ ብቁ የሒሳብና የኦዲት ባለሙያዎችን ማፍራት እንደሚገባ ጠቁመዋል።   ውይይቱም በኦዲት ጥራት የታዩ ክፍተቶችን በመለየት የጋራ መፍትሔ ለማስቀመጥ ያለመ መሆኑ ተገልጿል።    
በክልሉ በንግድና በገቢ ተቋማት የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በማረም ውጤታማ ሥራ ለማከናወን የተጀመረው ቅንጅታዊ ሥራ ይጠናከራል-ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Aug 10, 2026 305
ሆሳዕና፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በንግድና በገቢ ተቋማት የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በማረም ውጤታማ ሥራ ለማከናወን በቅንጅት የሚሰራው ሥራ እንደሚጠናከር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። በክልሉ ገቢዎች እና ንግድና ገበያ ልማት ቢሮዎች በህገ ወጥ የንግድ ቁጥጥር፣ ገበያ ማረጋጋትና የታክስ ተገዥነትን ማረጋገጥ አስመልክቶ የተዘጋጀ የንቅናቄ መድረክ በሆሳዕና ከተማ ተካሂዷል።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንደሻው ጣሰው (ዶ/ር) በመድረኩ ማጠቃለያ እንዳሉት በክልሉ በንግድ እና በገቢ ተቋማት ላይ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በማረም ውጤታማ ተግባራትን ለማከናወን በቅንጅት የሚሰሩ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። በተለይ በንግድ ሥርዓቱ የሚስተዋል ህገወጥነትን ለመከላከል በዘርፉ የወጡ ደንብና መመሪያዎችን ከሚያስፈጽሙ ባለድርሻ አካላት ጋር በቅርበት የሚሰራው ሥራ እንደሚጠናከር ገልጸዋል። በዚህም ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ በማድረግ የኑሮ ውድነቱን ለማባባስ የሚከናወኑ ህገወጥ ተግባራትን በመቆጣጠር ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የሚሰራው ሥራ ይጠናከራል ብለዋል። በተጨማሪም ክልሉ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የተጀመሩ የልማት ሥራዎችን ለማስቀጠልና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ተግባራት እንደሚጠናከሩ ነው እንዳሻው (ዶ/ር) የገለጹት። ለዚህም ገቢን በአግባቡ የመሰበሰብ ሂደቱን የሚያስተጓጉሉ ከተጨማሪ እሴት ታክስና ከደረሰኝ ገቢ አሰባሰብ ጋር የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ለማረም ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ሥራ ይሰራል ብለዋል። በዚህ ረገድ አመራሩ በህብረተሰቡ ተሳትፎ ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል የህዝብን ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ሊተጋ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል።   የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ሀላፊ ባዩሽ ተስፋዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት፤ በክልሉ በንግድ ምዝገባ፣ ፈቃድ አሰጣጥና እድሳት ላይ በተለያየ መንገድ የሚከሰቱ ችግሮችን ለመፍታት አገልግሎቱን የማዘመን ሥራ እየተሰራ ነው። በገበያ የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት አምራቹንና ሸማቹን የሚያገናኙ ከ100 በላይ ገበያዎችና ሌሎች መደበኛ የግብይት ማዕከላት ለማህበረሰቡ አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በክልሉ በንግድ ሥርዓቱ ላይ የሚስተዋሉ ህገ ወጥ አሰራሮችን በማረም ረገድ የተጀመሩ ተግባራትን ለማጠናከርም ቅንጅታዊ ሥራው እንደሚጠናከር ተናግረዋል፡፡ በክልሉ በበጀት ዓመቱ ከ35 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ ከማህበረሰብ የሚነሱ የልማት ጥያቄዎችን ለመፍታት ግብ ተጥሎ ወደ ተግባር መገባቱን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ሀላፊ ቀመሪያ ረሻድ ናቸው፡፡   ገቢን በአግባቡ የመስበሰብ ሂደቱን የሚያስተጓጉሉ ከተጨማሪ እሴት ታክስና ከደረሰኝ ገቢ አሰባሰብ ጋር የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ለማረም ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ሥራ ይጠናራል ብለዋል፡፡ የክልሉ ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነርና የወንጀልና ትራፊክ አደጋ መከላከል ዘርፍ ሀላፊ ኮሚሽነር አብርሃም ቲርካሶ በበኩላቸው በክልሉ ህገወጥ የንግድ እንቅስቃሴና የኮንትሮባንድ ዝውውርን ለመከላከል እየተሰራ ነው። በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮች እንዲታረሙ ከሚሽኑ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ህግ የማስከበር ሥራውን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያሳደገልን ነው
Aug 10, 2026 298
ጊምቢ፣ ነሐሴ4/2018 (ኢዜአ) ፡-በምዕራብ ወለጋ ዞን እየተተገበረ የሚገኘው የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንዳስገኘላቸው ነዋሪዎች ገለጹ። የ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃ-ግብር በኢትዮጵያ በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ ያለ ሀገራዊ የልማት ንቅናቄ ሲሆን፤ ዋና ዓላማውም በግብርናው ዘርፍ በዶሮ፣ በወተት፣ በማር፣ በበግና ፍየል ማድለብ እንዲሁም በዓሳ እርባታ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ነው። መርሃ-ግብሩ በቤተሰብ ደረጃ የምግብና የሥርዓተ-ምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ የሀገር ውስጥ ምርትን በማሳደግ፣ የገበያ አቅርቦትን በማሻሻል እና ለዜጎች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ በመፍጠር ረገድም ትልቅ ድርሻ አለው። በዚሁ መሠረት በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን የመርሃ-ግብሩን አፈጻጸም ውጤታማ ለማድረግ ሰፊ እንቅስቃሴ ሲደረግ ቆይቷል። በዞኑ የሚገኙ አርሶ አደሮችና የአካባቢው ነዋሪዎች በዘመናዊ መንገድ የዶሮ እርባታ፣ የወተት ላሞች እንክብካቤ እና የማር ንብ እርባታ ላይ በስፋት እንዲሰማሩ መደረጉ ተገልጿል። ይህ እንቅስቃሴም በየቤተሰቡ ደረጃ ንጹህ እና የተመጣጠነ ምግብ በቀላሉ እንዲገኝ አስችሏል፤ አርሶ አደሮችና ወጣቶች ከዘርፉ የሚያገኙትን ትርፍ ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንዲፈጥሩና የኑሮ ደረጃቸውን እንዲያሻሽሉም አድርጓል። በዞኑ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በመሳተፍ ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል የኢናንጎ ከተማ ነዋሪ አቶ ሂካ ኩመራ እና አለምነሽ አብዲ እንዳሉት አምስት የወተት ላሞች በማርባት በቀን በአማካይ 150 ሊትር ወተት እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በከተማ አስተዳደሩ በተፈጠረላቸው ድጋፍና ዕድል በወተት ላም እርባታ ዘርፍ መሰማራታቸው፣ የኑሮ ደረጃቸውን ለማሻሻልና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። ወይዘሮ ዲርቤ ሌሊሳ በበኩላቸው 300 እንቁላል ጣይ ዶሮዎችን በማርባት በሥራቸው ትርፋማ መሆን መቻላቸውን ገልጸዋል። በዚህም ለአካባቢው ማህበረሰብ እንቁላል በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ማድረጋቸውንና የራሳቸውን ገቢ ማሳደጋቸውን ገልጸው፤ በተጨማሪም ለልጆቻቸው የተመጣጠነ ምግብ ለማቅረብ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። ወጣት ሙቤ ቃሲም በበኩሉ ከቤተሰቦቹ ጋር በመሆን በ500 ዶሮዎች የጀመረው የእርባታ ሥራ አሁን ላይ ውጤታማ እያደረገው መሆኑን ገልጸዋል። የእንቁላል እና የሥጋ ዶሮዎችን ለገበያ በማቅረብ በሥራው ትርፋማ እየሆነ መምጣቱንም ተናግሯል።   የምዕራብ ወለጋ ዞን የኢናንጎ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዳንኤል በዳሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተማዋ የሕዝቡን የልማት ጥያቄዎች የመመለስ ሥራዎችን ከመስራት ጎን ለጎን የህብረተሰቡን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በተለይም በ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃ-ግብር ዝርያቸው የተሻሻሉ የወተት ላሞች፣ ዶሮዎች እና የንብ ቀፎዎች ለአካባቢው ነዋሪዎች እየቀረቡ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የምዕራብ ወለጋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት የእንስሳት ልማት እና ዝርያ ማሻሻያ ቡድን መሪ አቶ ገመቺስ ታደሰ፤ በ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃ-ግብር በርካታ ወገኖችን ተጠቃሚ ማድረግ ያስቻሉ ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል።   በተለይም ዝርያቸው የተሻሻሉ የወተት ላሞች አቅርቦትና በዶሮ እርባታ ልማት ላይ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃግብር 5 ነጥብ 7 ሚሊዮን የዶሮ ጫጩቶች ለአርሶ አደሮችና ወጣቶች የተሰራጩ ሲሆን፤ 5 ሺህ ላሞችን በማዳቀልም 90 ሚሊዮን 58 ሺህ ሊትር የወተት ምርት ማግኘት ተችሏል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪም በዞኑ በ‘ሌማት ትሩፋት’ መርሃ-ግብር አማካኝነት የዓሳ እርባታ መንደሮች በስፋት እየተገነቡ እንደሚገኙ አስረድተዋል።    
በአማራ ክልል ከዘንድሮ ዓመት የበልግ ሰብል ልማት ከሶስት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተሰበሰበ
Aug 10, 2026 342
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በበልግ ወቅት ከለማው ሰብል ከሶስት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የሰብል ልማት ባለሙያ ወይዘሮ እንዬ አሰፋ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በመኸር፣ በመስኖና በበልግ ልማት የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት እየተቻለ ነው። በበጋው ወቅትም የበልግ አብቃይ በሆኑ ዞኖች 247 ሺህ 367 ሄክታር መሬት በማልማት ከሶስት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል። የተገኘው ምርትም የገብስ፣ ስንዴ፣ አኩሪ አተር፣ ቦሎቄ፣ ጤፍ፣ ማሾና ሌሎች ሰብሎች መሆኑን ጠቁመው፤ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የሁለት ሚሊዮን ኩንታል ብልጫ አለው ብለዋል። ይህም አርሶ አደሩ የምግብ ዋስትናውን እያረጋገጠ እንዲመጣ ከማድረግ ባለፈ፤ ለኢንዱስትሪ ግብአትና ለወጭ ንግድ የሚሆን ምርት በማምረት ተጠቃሚ እንዲሆን እያስቻለ መሆኑን ተናግረዋል። በደቡብ ወሎ ዞን የተሁለደሬ ወረዳ አርሶ አደር ኢብራሂም አህመድ በሰጡት አስተያየት፤ በዘንድሮው የበልግ ዝናብ አንድ ሄክታር ተኩል ማሳቸውን ቦሎቄና ሽምብራ በመዝራት የተሻለ ምርት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ይህም በምግብ ራሴን እንድችል ከማድረግ ባለፈ ከምግብ ፍጆታ የተረፈውን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እንድሆን አስችሎኛል ብለዋል። የበልግ ዝናብ ስርጭቱ የተሻለ በመሆኑ በግማሽ ሄክታር መሬት ካለሙት የገብስ ሰብል 15 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ በሰሜን ሸዋ ዞን የጣርማ በር ወረዳ አርሶ አደር አሰፋ መኮነን ናቸው። በ2017 በጀት ዓመት በክልሉ በበልግ ሰብል ከለማው ከ146 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ከአንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
በአዳማ ከተማ ከ25 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን መሬት ታርሶ በዘር ተሸፍኗል
Aug 10, 2026 266
አዳማ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፡-በአዳማ ከተማ ከልማት ሥራዎች ጎን ለጎን ከ25 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን መሬት ታርሶ በዘር መሸፈኑን የከተማዋ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። አዳማ ከኦሮሚያ ክልል ዋነኛ የኢኮኖሚ፣ የኢንዱስትሪ እና የትራንስፖርት ማዕከላት መካከል አንዷ በመሆኗ ፈጣን የከተማ ማስፋፋትና የህዝብ ቁጥር እድገት የሚታይባት ከተማ ናት። የከተማዋ የቆዳ ስፋትና የመሰረተ ልማት ዝርጋታ በየጊዜው እያደገ ቢመጣም፣ ከተማን ከአካባቢ ጥበቃ እና ከምግብ ዋስትና ጋር አጣጥሞ ማስኬድ አስፈላጊ ነው። ይህ እርምጃ የከተሞች ህዝብ ቁጥር መጨመርን ተከትሎ የሚከሰተውን የምግብ ፍላጎት ለማሟላት እና አትክልትና ሰብል ምርቶች አቅርቦትን ጨምሮ የዋጋ ንረትን ለመቀነስ፣ እንዲሁም ለወጣቶች እና ለሴቶች በከተማ ግብርና እና በዘመናዊ የእርሻ ስራዎች የስራ እድል ለመፍጠር ታስቦ የሚተገበር ይሆናል። የአዳማ ከተማ ግብርና ጽሕፈት ቤት እንደገለፀው ከ25 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑ፣ ከተማዋ የማኑፋክቸሪንግ እና የንግድ ማዕከልነቷን እንደጠበቀች የግብርና ምርታማነቷንም ጎን ለጎን ለማሳደግ እያደረገች ያለውን ጥረት የሚያሳይ ነው።   የጽሕፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ አለሙ ቂልጡ ለኢዜአ እንደገለጹት በ2018/19 የምርት ዘመን የከተማዋን አርሶ አደር ምርትና ምርታማነት ለመጨመር በተሻለ ደረጃ የምርት ማሳደጊያ ግብዓት ቀርቧል። ከምስራቅ ሸዋ ዞን አዳማ ወረዳና ሉሜ ወረዳ 28 የገጠር ቀበሌዎችን በማጠቃለል እንደገና የተደራጀችው አዳማ፤ በሺህዎች የሚቆጠሩ አርሶ አደሮች ወደ ከተማዋ መቀላቀላቸውንም ሃላፊው ገልጸዋል። በዚህም ከተማዋ የነበራት የእርሻ መሬት ከእጥፍ በላይ ማደጉን የገለጹት አቶ አለሙ፤ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የእርሻ አሰራር ስርዓቱ በቴክኖሎጂና በሜካናይዜሽን የታገዘ እንዲሆን በተደረገው ጥረት ውጤት እየተመዘገበ ነው ብለዋል።   ለዘንድሮ የመኽር እርሻ ልማት በአስተዳደሩ 20 የእርሻ ትራክተሮች ተገዝተው ለአርሶ አደሩ መሰጠቱን ገልጸው፤ እስካሁን 25ሺህ 154 ሄክታር መሬት በስንዴ፣ ጤፍ፣ ቦቆሎና ጥራጥሬን ጨምሮ በዋና ዋና ሰብሎች ተሸፍኗል ብለዋል። በመኽር እርሻው ከ50ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘርና ፀረ አረም መድሃኒቶች ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱንም አቶ አለሙ ጨምረው ገልጸዋል። በተጨማሪም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የከተማዋን አርሶ አደር ህይወት ከመሰረቱ ለመለወጥ ከዋና ዋና የሰብል ልማት ባለፈ ተጨማሪ ገቢ ማስገኘት የሚችሉና ከውጭ የሚገቡ የግብርና ምርቶችን መተካት በሚችሉት የፍራፍሬ ልማት ላይ በትኩረት እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። በዚህም በከተማ አስተዳደሩ ከ100 ሄክታር በላይ መሬት ላይ አቮካዶ፣ ብርትኳን፣ ሎሚ፣ ፓፓየ፣ ዘይቱንና ማንጎ በስፋት እየለማ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በተለይም የአዋሽ ወንዝን ጨምሮ የመስኖ ውሃ ተቋማትን በመጠገንና የውሃ መሳቢያ ሞተሮችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ በዓመት ከሶስት ጊዜ በላይ የማምረት ሂደት ባህል እንዲሆን እንደሚሰራም ተናግረዋል።  
ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ የህዝብን የልማት ጥያቄ የመመለስ ተግባራት ይጠናከራሉ - ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Aug 10, 2026 279
ሆሳዕና፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ የህዝብን የልማት ጥያቄ የመመለስ ተግባራት እንደሚጠናከሩ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። የክልሉ ገቢዎች እና ንግድና ገበያ ልማት ቢሮዎች በሕገ-ወጥ የንግድ ቁጥጥር፣ ኑሮን በማረጋጋትና የታክስ ሕግ ተገዢነትን በማረጋገጥ ዙሪያ የተዘጋጀ የንቅናቄ መድረክ በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ የሕዝቡን የልማት ጥያቄዎች የመመለስ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ የገቢ አቅምን በማሳደግ የከተሞችን ገጽታ የመቀየር፣ የመሠረተ ልማት ተደራሽነትን የማስፋትና የማህበረሰቡን ሕይወት ለማሻሻል በተከናወኑ ተግባራት የተመዘገቡ ስኬቶች ይጠናከራሉ ብለዋል። በሌላ በኩል በክልሉ የንግድ ሥርዓቱን በማዘመን የተሳለጠ አሠራር መዘርጋት አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል። ለዚህም ሕገ-ወጥነትን የመከላከል፣ የግብይት ማዕከላትን የማስፋፋት፣ ምርትን በበቂ ሁኔታ የማቅረብ፣ የዋጋ ንረትን የመቆጣጠርና የሸማች ማኅበራትን የማጠናከር ሥራዎች እንደሚከናወኑ አክለዋል፡፡   በዘርፉ የሚከናወኑ ተግባራት ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን ለማሳለጥና የኑሮ ውድነቱን ለማረጋጋት ወሳኝ በመሆናቸው፣ መስተዳድሩ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅታዊ ሥራ ማጠናከር የትኩረት አቅጣጫው ማድረጉንም ገልጸዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር የመንግሥትና የፓርቲ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
ኦዲተሮች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን በመተግበር ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል
Aug 10, 2026 266
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ) ፦ ኦዲተሮች ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን በመተግበር ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድ አመለከተ። ቦርዱ በኦዲት ጥራት የግምገማ ውጤቶች ዙሪያ ከኦዲተሮች ጋር እየተወያየ ይገኛል። የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ አጎናፍር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኦዲተሮች ለሂሳብ ሪፖርቶች ጥራት መጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል። የሂሳብ ሪፖርቶችን ጥራት የሚያስጠብቁ ዓለም አቀፍ ደረጃዎችን ጠብቆ መስራት ላይ ውስንነቶች መኖራቸውን የግምገማ ውጤቱ እንደሚያመላክት ጠቁመው ኦዲተሮች ይህንን ክፍተት ለመሙላት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ነጻ እና ገለልተኛ ሆኖ በሃላፊነት መስራት ከኦዲተሮች የሚጠበቅ ሌላው ሙያዊ ግዴታ መሆኑን ጠቁመው የስነ ምግባር መርሆዎችን ጠብቆ መስራት እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። ጥራቱን የጠበቀ የሂሳብ ሪፖርት ኢንቨስትመንት ለመሳብ፣ ለታክስ ስርአት ውጤታማነት እንዲሁም ለሀገር ኢኮኖሚ መሳለጥ ትልቅ ሚና እንዳለውና ለስኬታማነቱ የኦዲተሮች ሙያዊ ደረጃዎችን ጠብቆ መስራት ቁልፍ ድርሻ አለው ብለዋል። እንደ ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ ገለጻ፤ ኢትዮጵያ ወደ ካፒታል ገበያ ስርአት እየገባች በመሆኑ ጥራትና ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የኦዲት ስርአት አስፈላጊ ነው። የኢትዮጵያ ሂሳብ አያያዝ እና ኦዲት ቦርድም የኦዲተሮችን አቅም በመገንባት ለዘርፉ ውጤታማነት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የውይይት መድረኩ በኦዲት ጥራት ክፍተቶች ዙሪያ በመመካከር የጋራ መፍትሔ ለማመላከት መሆኑን ጠቁመዋል።
በደቡብ ወሎ ዞን እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ በመቀየር ለእንቅስቃሴና ለልማት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Aug 10, 2026 447
ደሴ ፤ ነሐሴ 4/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ በመቀየር እንዲነቃቁ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የዞኑ ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የመሰረተ ልማት ቡድን የኮንስትራክሽን አስተዳደር መሃንዲስ አደም መሃመድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በሐይቅ፣ ጊምባ፣ መካነሰላም፣ ሀርቡ፣ ወረኢሉ፣ አቀስታ እና ደጎሎ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ እየተካሔደ ነው።   በነዚሁ አካባቢዎች በመገንባት ላይ ካለው 6 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ ውስጥም ከሁለት ኪሎ ሜትር በላይ የሚሆነው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑን ተናግረዋል። የኮሪደር ልማቱ ከተሞችን በማስዋብና ገጽታቸውን በመቀየር እንዲነቃቁ ከማድረጉ ባለፈ ለነዋሪዎች፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል። ቀሪውን ሥራ በፍጥነትና በጥራት አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት ሰፊ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም አክለዋል። ልማቱ የእግረኛና የብስክሌት መንገዶችን፣ መዝናኛዎችንና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን ያካተተ በመሆኑ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረጉን ነው የጠቀሱት። ማሕበረሰቡ ለግንባታ ስራው በገንዘብ፣ በጉልበትና ቁሳቁስ በማቅረብ ከፍተኛ ተሳትፎ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። የሐይቅ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ እናትነሽ በሽር በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማቱ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉ ከተማዋን ከማነቃቃቱ በላይ ለነዋሪዎች ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል። በተለይም የእግረኛ፣ የተሽከርካሪና የብስክሌት መንገዶችን እንዲሁም መዝናኛዎችን ማካተቱ የትራፊክ አደጋን በማስቀረት በነጻነት ለመንቀሳቀስ አስችሎናል ነው የሚሉት።   ሌላው የዚሁ ከተማ ነዋሪ ሸህ ጀማል ለይሱ፤ ልማቱ የከተማዋን ገጽታ በማሳመርና በማስዋብ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ነው ያብራሩት።   ህብረተሰቡ በገንዘብ፣ በቁሳቁስና በጉልበት ያደረገው አስተዋጽኦ የግንባታ ስራው በፍጥነትና በጥራት ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ ማድረጉን ገልፀዋል።
በጋምቤላ ክልል በተያዘው የመኸር ወቅት ከ86 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰሊጥ ለምቷል
Aug 10, 2026 271
‎ጋምቤላ፤ ነሐሴ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በተያዘው የመኸር ወቅት ከ86 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሰሊጥ ልማት መከናወኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ አስታወቀ። የጋምቤላ ክልል ሰፊና ለም መሬት፣ በቂ የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር የውሃ ሀብት እንዲሁም ለተለያዩ የግብርና ምርቶች ተስማሚ የሆነ አየር ንብረት ያለው አካባቢ ነው። ክልሉ በተለይም ለቅባት ሰብሎች አመቺ በመሆኑ በሀገሪቱ የግብርና ኢንቨስትመንት ከተመረጡ ዋና ዋና አካባቢዎች አንዱ ያደርገዋል። ባለፉት ዓመታት በክልሉ የሚካሄደው የቅባት ሰብሎች ልማት በዋናነት በባህላዊ መንገድ በአርሶ አደሮችና በጥቂት ባለሃብቶች የተወሰነ የነበረ፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን በዘመናዊ የግብርና ግብአቶች እና በሜካናይዜሽን ታግዞ በፍጥነት እያደገ ይገኛል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ኡጀሉ ኡሞድ ለኢዜአ እንደገለጹት ክልሉ የቅባት ሰብሎችን ጨምሮ ለሁሉም የግብርና ልማት ምቹ ስነ- ምህዳር ያለው አካባቢ ነው። ‎ክልሉ ለሁሉም የግብርና ልማት የተመቸ ከመሆኑ ጋር ተያይዞም የቅባት እህሎችን ጨምሮ በሌሎች ሰፋፊ የግብርና ልማት ለመሰማራት በርካታ ባለሃብቶች ወደ ክልሉ እየገቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ‎በክልሉ በዘንድሮው የመኸር እርሻ በባለሃበቶችና በአርሶ አደሮች ከ86 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰሊጥ መልማቱን ገልጸዋል። ‎በክልሉ በዘንድሮው የመኸር ወቅት የለማው መሬት ከቀዳሚው ዓመት ጋር ሲነፃፀር ከ20 ሺህ ሄክታር በላይ ብልጫ ያለው መሆኑን አስረድተዋል። ‎በክልሉ ከለማው ሰሊጥም ከ516 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ሊሰበሰብ እንደሚችል ጠቁመው፤ አሁን ላይ ያለው የሰብሉ ቁመና የተሻለ ስለሆነ ከተጠበቀው በላይ ምርት ሊገኝ ይችላል የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል። ‎በክልሉ አቦቦ ወረዳ በሰሊጥ ሰብል ልማት ከተሰማሩት ባለሃብቶች መካከል አቶ እየሩስ ዓለሙ በሰጡት አስተያየት የዘንድሮው ክረምት የዝናብ ስርጭት ቀለል ያለ በመሆኑ ለሰሊጥ ሰብል ምቹ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በ120 ሄክታር መሬት ላይ ያለሙት ሰብል ደርሶ በመሰብሰብ ሂደት ላይ መሆኑን ጠቁመው የዘንድሮው የሰሊጥ ምርት በብዛትም ሆነ በጥራት የተሻለ መሆኑን ተናግረዋል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም