ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
አገልግሎቱ የውጭ ባለሀብቶች በሚሰማሩባቸው የትኛውም የሥራ መስኮች አስተማማኝ የፀጥታና ደኅንነት ምህዳር እንዲፈጠር የሚያግዝ ስምሪት እያከናወነ ይገኛል
Jul 29, 2026 73
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ)፦ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የውጭ ባለሀብቶች በሚሰማሩባቸው የትኛውም የሥራ መስኮች አስተማማኝ የፀጥታና ደኅንነት ምህዳር እንዲፈጠር የሚያግዝ ስምሪት እያከናወነ እንደሚገኝ የአገልግሎቱ ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) አስታወቁ። የአሜሪካ መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ እና አፍሪካ ምክትል ረዳት ሚኒስትር ማርክ ሚቸል ሀገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ስትራቴጂክ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በትብብር ለመሥራት ያላትን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ በላከው መረጃ እንዳመለከተው፤ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) የአሜሪካ መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ እና አፍሪካ ምክትል ረዳት ሚኒስትር ማርክ ሚቸል ከተመራ ልዑክ ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተዋል። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ ተቋሙ በኢትዮጵያ ለኢንቨስትመንት፣ ለንግድና ለሌሎችም የውጭ ባለሀብቶች ለሚሰማሩባቸው የትኛውም የሥራ መስኮች አስተማማኝ የፀጥታና ደኅንነት ምህዳር እንዲፈጠር የሚያግዝ ስምሪት እያከናወነ ይገኛል፡፡ ይህም ለአሜሪካ የቢዝነስ ማኅበረሰብ መተማመን የሚፈጥር መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በየጊዜው ሲያጋጥሙ የነበሩ የፀጥታ ስጋቶችን በማስወገድ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ደኅንነትንና ሰላምን የማረጋገጥ ሰፊ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥትም ቀጣናዊ መረጋጋት ለማስፈን የጋራ ተጠቃሚነትን መርህ ያደረጉ ስትራቴጂዎች በመንደፍና ቁርጠኛ አቋም በመያዝ እየተገበረ መሆኑን ገልጸው፤ የመረጃና ደኅንነት ተቋሙም በዚህ በኩል ያለውን ዝግጁነት ጠቁመዋል፡፡ የአሜሪካ መንግሥት የመካከለኛው ምሥራቅ እና አፍሪካ ምክትል ረዳት ሚኒስትር ማርክ ሚቸል በበኩላቸው፤ ሀገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ስትራቴጂክ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በትብብር ለመሥራት ያላትን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል፡፡ ረዳት ሚኒስትር ማርክ ሚቸል የአሜሪካ ኩባንያዎች በሀገሪቱ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ተሰማርተው መስራት በሚችሉበት ሁኔታ ላይ ማብራሪያ እንደሰጡና ለዚህም አስቻይ ሁኔታዎች መኖሩን እንደገለፁ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ የላከው መረጃ አመልክቷል።
በክልሉ የሕዝቦችን አብሮነት በማጠናከር የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ይሰራል
Jul 29, 2026 122
ሆሳዕና ፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ) :- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሕዝቦችን አብሮነት በማጠናከር የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። በክልሉ የ2018 በጀት ዓመት የፓርቲና የመንግሥት ሥራዎች አፈጻጸም እና የ2019 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ ክልላዊ የከፍተኛ አመራሮች የውይይት መድረክ በሆሳዕና ከተማ ተካሄዷል። በወቅቱም የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንደገለፁት፤ በክልሉ የሕዝቦችን አብሮነት በማጠናከር የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ይሰራል። ርዕሰ መስተዳድሩ አክለውም፤ የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ተግባራት በተያዘው በጀት ዓመትም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። ለዚህም አመራሩ የጋራ ትርክትን በመገንባትና ሙሉ ጊዜውን ሰጥቶ በመሥራት ለአካባቢው ፈጣን ልማት መረጋገጥ መትጋት እንዳለበት አሳስበዋል። በዋናነትም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የኑሮ ውድነትን በማረጋጋት፣ የሥራ ዕድል በመፍጠርና በሌሎች ኢኮኖሚያዊ መስኮች የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ የተከናወኑ ተግባራት በቀጣይም ልዩ ትኩረት ይሰጣቸዋል ብለዋል። ለሕብረተሰቡ የመልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት እንዲያስችል የገቢ አማራጮችን በማስፋትና ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ መሰብሰብ እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር ተያይዞ የሚስተዋሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በማረምና ጠንካራ የድጋፍና ክትትል ሥራ በማከናወን ተጨባጭ ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እንደሚሠራም ገልጸዋል። በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ዲላሞ ኦቶሬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የክልሉ አመራር በፓርቲው መርህ ላይ ተመስርቶ ማኅበረሰቡን ማገልገል እንዳለበት ተናግረዋል። የተረጋጋ የፖለቲካ ምህዳር ከመፍጠር ባለፈ የማኅበረሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጡ ተግባራት ላይ ትኩረት ሰጥቶ መሥራት እንደሚገባም ገልጸዋል። ማኅበረሰቡን ያሳተፉ የንቅናቄ ተግባራትን በማከናወን እየተመዘገቡ የሚገኙ ስኬቶችን ማጠናከር እንደሚጠበቅም ኃላፊው አመልክተዋል።
በክልሉ በግብርና ልማትና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ የተገኙ ስኬቶችን ለማስቀጠል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው
Jul 29, 2026 167
ሀረር፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ) :- በሐረሪ ክልል በግብርና ልማትና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ የተገኙ ስኬቶችን ለማስቀጠል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ሃላፊ ሮዛ ኡመር ተናገሩ። በክልሉ የ2018 የግብርና ልማት እቅድ አፈጻጸምና የ2019 የግብርና ልማት መሪ እቅድ ላይ የውይይት መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ሃላፊ ሮዛ ኡመር፤ በክልሉ ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት የመውጣት ጥረት ተጨባጭ ውጤቶች እየተመዘገቡበት መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በገጠር ወረዳዎች በመስኖ ልማት የተከናወኑ የልማት ስራዎች ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በቤተሰብ ደረጃ ጭምር የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ ያስቻሉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር በተለይም የእንስሳት ተዋጽኦ እንዲሁም የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ትልቅ እመርታ የተገኘበት ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም ከተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ባሻገር የምግብ ዋስትና መሰረት መሆኑን አንስተው በተያዘው በጀት ዓመትም በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን ተናግረዋል። በግብርና ልማትና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ የተገኙ ስኬቶችን ለማስቀጠል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አንስተው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። የቢሮው የእቅድና ክትትል ዳይሬክተር ሚልኬሳ አህመድ፤ በበጀት ዓመቱ ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሰፋፊ ስራዎች ተከናውነዋል ውጤትም አስገኝተዋል ብለዋል። በግብርና ዘርፍ በሰብል ልማት፣ የአትክልት እና ፍራፍሬ ምርታማነት እንዲሁም የሌማት ትሩፋት ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን ጠቅሰዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል የግብርና ባለሙያው መሳይ ስለሺ፤ በክልሉ የአርሶ አደሩ ምርታማነትና ተጠቃሚነት ከፍተኛ መሻሻል ማሳየቱን አንስተዋል። በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና እንክብካቤ እንዲሁም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እመርታዊ ለውጥ እያስገኙ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በመድረኩ በ2018 በጀት ዓመት በግብርና ልማት ተግባራት አበረታች ስራ ላከናወኑ የወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት፣ የግብርና ባለሙያዎችና ሌሎች አካላት እውቅና ተሰጥቷል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በመኸር እርሻ እስካሁን ከ385 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Jul 29, 2026 187
ደብረ ማርቆስ ፤ሃምሌ 22/2018(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን በመኽር ወቅቱ እስከሁን ከ385 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ስብሎች ዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ እምቢአለ አለኽኝ ለኢዜአ እንደገለጹት በያዝነው የመኸር ወቅት ከእለት ፍጆታ ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት በትኩረት እየተሰራ ነው። በምርት ወቅቱ ከ669 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት 26 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል። እስካሁን በተደረገ ጥረት ከ385 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ታርሶ በዘር መሸፈኑን ተናግረዋል ። በቆሎ፣ ገብስ፣ ስንዴ፣ ባቄላ፣ በሎቄ፣ ማሽላ፣ የቢራ ገብስ፣ ጤፍና ሌሎች ገበያ ተኮር ሰብሎች መዘራታቸውን ጠቅሰዋል። በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥም ከ90 በመቶ በላይ የሚሆነውን በመስመር እንዲሁም ከ229 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው ደግሞ በኩታገጠም የተዘራ መሆኑን አብራርተዋል። ምርታማነትን ለማሳደግ በተደረገ ጥረትም ከ660 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ መዋሉን ተናግረዋል። የመኸር እርሻው ከ390 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ እየተካሄደ መሆኑን አስታውቀዋል። በዞኑ የጎዛምን ወረዳ የሸበልማ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አንሙት የሻንበል እንደገለጹት የክረምቱን ዝናብ በመጠቀም ከአንድ ሄክታር በላይ መሬታቸውን በበቆሎና በስንዴ ሰብል መሸፈናቸውን ገልጸዋል። ምርታማነታቸውን ለማሳደግም የግብርና ባለሙያን ምክረ ሃሳብ በመከተል ማዳበሪያ በመጠቀም፣ በኩታ ገጠምና በመስመር መዝራታቸውን አስረድተዋል። የቀበሌው ነዋሪ አርሶአደር ይበልጣል ካሴ በበኩላቸው ባቄላ፣ ገብስና በቆሎ ሰብሎችን ቀድመው መዝራታቸውን ጠቁመው ጤፍ ለመዝራት በዝግጅት ላይ መሆናቸውን አስረድተዋል።
በክልሉ 51 የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታን በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ማድረግ ተችሏል
Jul 29, 2026 172
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ):-በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 51 የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታቸው ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የመስኖ ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ አየልኝ መሳፍንት ለኢዜአ እንዳሉት፤ በክልሉ ዘመናዊ የመስኖ አውታሮችን ግንባታ በማስፋት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት እየተሰራ ይገኛል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም አርሶ አደሩን ከባህላዊ አሰራር በማላቀቅ በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ ማምረት የሚችልበትን እድል ከማስፋት አንፃር የተሻለ ስራ ማከናወን ተችሏል ነው ያሉት። ለመስኖ ልማት የሚውሉ አካባቢዎችን በጥናት ከመለየት ባለፈ ወደ ግንባታ በማስገባት አርሶ አደሩ የዘመናዊ መስኖ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆን ማድረግ መቻሉንም አብራርተዋል። በተቀናጀ መንገድ በተደረገ ጥረትም 90 የመስኖ ፕሮጀክቶችን ወደ ግንባታ ማስገባት መቻሉን ጠቅሰው፤ ከእነዚህ ውስጥ 51 የሚሆኑትን በማጠናቀቅ ለልማት ስራ እንዲውሉ ለማድረግ ተችሏል ነው ያሉት። ግንባታቸው የተጠናቀቁ የመስኖ ፕሮጀክቶችም ከ3 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት ማልማት ያስቻሉ ሲሆን ከ 7 ሺህ 500 በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሆኑም ገልፀዋል። በተጨማሪም ከ30 ሺህ ሄከታር በላይ መሬት ማልማት የሚችሉ 99 የመስኖ ፕሮጀክቶች ጥናትና ዲዛይንን በማጠናቀቅ ለግንባታ ስራ ዝግጁ ማድረግ እንደተቻለ ተናግረዋል። የመስኖ አውታሮችን በማስፋት የአርሶ አደሩን ትርፍ አምራች በማድረግ የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባሻገር ኢኮኖሚያዊ አቅሙን የማሳደግ ስራ ታሳቢ ተደርጎ እየተከናወነ ነው። እንዲሁም እንደ ሀገር በምግብ እህል ራስን የመቻል ግብ እንዲሳካ በሚያግዝ አግባብ እየተከናወነ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ለመስኖ ተቋማት ግንባታና ተያያዥ ስራዎች ከ1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ ወጭ መደረጉንም ምክትል ቢሮ ኃላፊው አስታውቀዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም ቀደም ሲል ግንባታቸው ተጀምሮ ያልተጠናቀቁ እና አዳዲስ ፕሮጀክቶችን ወደ ግንባታ በማስገባት ዕቅድ ተይዞ ወደ ስራ እየተገባ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ በመስኖ መልማት የሚችል ከ 2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት እንዳለም ከቢሮው የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
በባሌ ዞን በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎች በተሞክሮነት የሚወሰዱ ናቸው
Jul 29, 2026 267
ሮቤ፣ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ)፦በባሌ ዞን በግብርናው ዘርፍ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎች በተሞክሮነት የሚወሰዱ መሆናቸውን የብልጽግና ፓርቲ የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን የመስክ ምልከታ እያካሄዱ ነው። አመራሮቹ ''ውጤታማ ተግባቦት ለጠንካራ ፓርቲ''በሚል መሪ ሐሳብ ለሁለት ቀናት በባሌ ሮቤ ሲያካሂዱት የነበረውን የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ግምገማ መድረክ ካጠናቀቁ በኋላ ነው የመስክ ምልከታውን የጀመሩት። በብልፅግና ፓርቲ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት፤ በዞኑ የአርሶ አደሩን ሕይወት ለማሻሻል በግብርናው መስክ እየተከናወኑ የሚገኙ ሥራዎች በተሞክሮነት የሚወሰዱ ናቸው። በተለይ አርሶ አደሩ የተሻሻሉ የግብርና አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ በኩታ ገጠም ልማት እያከናወነ የሚገኘውን ጥረት በማሳያነት አቅርበዋል። እንዲሁም ዞኑ ዝናብና የሌሎች የውኃ አማራጮችን በመጠቀም በዓመት ሁለት ጊዜና ከዚያ በላይ ማልማት የሚቻልበት መሆኑን በመስክ ምልከታው ማረጋገጣቸውን ገልጸዋል። በየደረጃው የሚገኙ አርሶ አደሮች ከሚያለሙት ልማት ተጠቃሚ በመሆን፣ ኮምባይነርና ትራክተር በመግዛት ወደ ግብርና ሜካናይዜሽን እየተሸጋገሩ መምጣታቸውንም ተናግረዋል። ይህም በሀገር አቀፍ ደረጃ የግብርናውን ዘርፍ ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የገጠር ሽግግርን ለማፋጠን ያለው እገዛ ከፍተኛ መሆኑንም አክለዋል። የብልፅግና ፓርቲ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ አመራሮችና ባለሙያዎች የመስክ ምልከታ የዞኑን ነባራዊ ሁኔታ በመረዳትና በማስተዋወቅ፣ ወደየአካባቢያቸው ሲመለሱ የቀሰሙትን ልምድ እንዲያሰፉ ዕድልን ይፈጥራል ብለዋል። በዞኑ በዘንድሮ የበልግ ወቅት ከ240 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል ዘሮች የተሸፈነ ሲሆን፣ ከልማቱም ከ8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ የገለጹት ደግሞ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሀኪም አልይ ናቸው። በተለያዩ የሰብል ዘሮች እየለማ ከሚገኘው ልማት 80 በመቶ የሚሆነው በሜካናይዜሽን በመታገዝ በኩታ ገጠም አሰራር የለማ መሆኑንም ተናግረዋል። በዞኑ በመኸር፣ በበልግና በመስኖ አማራጮች ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚለማ ሲሆን፣ ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ዓመታዊ ምርት እንደሚመረትም አመልክተዋል። ለዚህም በልዑካን ቡድኑ የተጎበኘው የበጋ ስንዴ ልማት አንዱ ማሳያ መሆኑን ያነሱት ዋና አስተዳዳሪው፤ ጉብኝቱ በዞኑ የሚገኙ አማራጮች ይበልጥ እንዲተዋወቁ ዕድል መፍጠሩንም ገልጸዋል። የአመራር አባላቱ በሮቤ ከተማ መደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ ''ተስፋን እንትከል'' በሚል መሪ ሀሳብ ዐሻራቸውን ያኖሩ ሲሆን፣ ጉብኝታቸውን በመቀጠልም የአካባቢውን የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎች እንደሚጎበኙም ታውቋል።
በክልሉ በሰላም፣ በልማትና መልካም አስተዳደር የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ስራዎች ተከናውነዋል-ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰዉ (ዶ/ር)
Jul 29, 2026 164
ሆሳዕና ፤ ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት አመት በሰላም፣ በልማትና መልካም አስተዳደር የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ስራዎች መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። "ሁሉ አቀፍ እመርታ ፣ ለሁለንተናዊ ከፍታ" በሚል መሪ ሀሳብ በክልሉ የ2018 በጀት ዓመት የፓርቲና የመንግስት ስራዎች አፈፃፀምና የ2019 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ የከፍተኛ አመራሮች የዉይይት መድረክ በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ነው። ርዕስ መስተዳድሩ በወቅቱ ባደረጉት ንግግር በክልሉ በ2018 በጀት ዓመት በፓርቲና በመንግሥት ስራዎች አፈፃፀም ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል። በሰላም፣ በልማትና መልካም አስተዳደር የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ስራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል። የህዝቦችን አብሮነት በማጠናከር ክልሉን የህብረ ብሄራዊነት ተምሳሌት ለማድረግ በተሰሩ ስራዎች ውጤት መመዝገቡን አመልክተዋል። በበጀት ዓመቱ የተገኙ ስኬቶችን ማጠናከርና የተስተዋሉ ጉድለቶችን በማረም ቀጣይ አቅጣጫ ማስቀመጥ የመድረኩ ዋና ዓላማ ስለመሆኑም ገልጸዋል። በመድረኩ የክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ፋጤ ሰርሞሎ ፣ በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ዕህፈት ቤት ሀላፊ ዲላሞ ኦቶሬ (ዶ/ር) ጨምሮ የክልል ፣ የዞን ፣ የልዩ ወረዳ ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች እየተሳተፉ ነው።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 9 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ አገኘ
Jul 29, 2026 295
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ) :-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 9 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን የግሩፑ ዋና ስራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ። አየር መንገዱ በ2018 በጀት ዓመት ውጤማ የስራ እንቅስቃሴ ማድረጉንም ዋና ስራ አስፈጻሚው ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው በሰጡት መግለጫ እንዳሉት፤ አየር መንገዱ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 9 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ አግኝቷል። ገቢው ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ20 በመቶ ብልጫ እንዳለው ጠቅሰው፤ በ2018 በጀት ዓመት ከተያዘው ዕቅድ ጋር ሲነጻጸር የ9 በመቶ ብልጫ አለው ብለዋል። አራት አዳዲስ ዓለም አቀፍ የበረራ መዳረሻዎች መክፈቱን ጠቁመው፤ 20 ነጥብ 7 ሚሊዮን መንገደኞችን ማጓጓዙን ተናግረዋል። 22 የነበሩ የሀገር ውስጥ መዳረሻዎች ወደ 25 ከፍ እንዲል መደረጉን ጠቁመው፤ ይህም የሀገር ውስጥ አገልግሎት አቅም ከፍ ያደረገ ነው ብለዋል። 897 ሺህ ቶን ጭነት የማጓጓዝ አገልግሎት መስጠቱን ገልጸው፥ ይህም ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ16 በመቶ ብልጫ እንዳለው አስረድተዋል። እንደ አቶ መስፍን ገለጻ አየር መንገዱ በበጀት ዓመቱ 9 አዳዲስ አውሮፕላኖች በግዥ እና በኪራይ ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉ የተሻለ ውጤት እንዲመጣ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ጠቅሰዋል።
በሸገር ከተማ ባለፈው በጀት ዓመት ከቱሪዝም ዘርፍ ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተገኝቷል
Jul 29, 2026 178
ሸገር፣ ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ)፡-በሸገር ከተማ በ2018 በጀት ዓመት ከቱሪዝም ዘርፍ ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን የከተማው አስተዳደር አስታወቀ። የሸገር ከተማ አስተዳደር ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ቢንያም ፀጋዬ በ2018 በጀት ዓመት በከተማው ያለውን የተፈጥሮ እና ሰው-ሰራሽ የቱሪዝም መስህቦችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በከተማው የቱሪዝም መሠረተ ልማትን በማስፋፋት ወደ ከተማዋ የሚደረገውን የቱሪስቶች ፍሰት ለመጨመር የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቁመዋል። በከተማዋ ጥንታዊና ታሪካዊ የሃይማኖት ተቋማትን፣ በገፈርሳ ሐይቅ የሚካሄዱ የእሬቻና መልካ አቴቴን የመሰሉ የኦሮሞ ህዝብ በዓላት የሚከበሩባቸውን ስፍራዎች በማልማት የቱሪስቶች ፍሰት እንዲጨምር ጥረት መደረጉን ተናግረዋል። በተጨማሪም የተለያዩ እንስሳትና አእዋፋት የሚገኙበት የኤግዱ እላላ፣ ሌሎች ውብ ተራሮችና አስደናቂ የመሬት አቀማመጦችን ለቱሪስት ምቹ በማድረግ፣ የቱሪስቶችን ፍሰት ከማሳደግም ባለፈ የቆይታ ጊዜያቸውን እንዲያራዝሙ መደረጉን ገልጸዋል። በዚህም በ2018 በጀት ዓመት 500 ሺህ የሀገር ውስጥ ጎብኚዎችን ለማስተናገድ በማቀድ በተደረገው እንቅስቃሴ ከ1 ሚሊዮን በላይ በሚሆኑ ጎብኚዎች ከዕቅድ በላይ መፈፀም መቻሉን ተናግረዋል። እንዲሁም ከ25 ሺህ በላይ የሚሆኑ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች ከተማዋን መጎብኘታቸውን ኃላፊው ጠቁመው፣ በአጠቃላይ ከቱሪዝም ዘርፉ ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ተናግረዋል። በከተማዋ በተከናወኑ ተግባራት ዘርፉ ገቢን ከማስገኘት ባለፈ ለዜጎች በርካታ የሥራ እድሎችን እየፈጠረ መሆኑንም አብራርተዋል። በ2019 በጀት ዓመትም በከተማዋ የሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎችን በማልማትና በማስፋፋት፣ የከተማዋን የቱሪስት ፍሰት ለመጨመርና የቆይታ ጊዜ ለማራዘም የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ መሆናቸውንም አስረድተዋል።
በደቡብ ጎንደር ዞን በሩዝ ሰብል ለማልማት ከታቀደው ውስጥ 91 በመቶውን ለማሳካት ተችሏል- መምሪያው
Jul 29, 2026 172
ጎንደር፤ ሐምሌ 22 /2018 (ኢዜአ) ፡-በደቡብ ጎንደር ዞን በያዝነው ክረምት በሩዝ ሰብል ለማልማት ከታቀደው 107 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ 91 በመቶውን በዘር መሸፈን መቻሉን የዞኑ ግብርና መመሪያ አስታወቀ። የመመሪያው ኃላፊ አቶ የሺጥላ አፍቃዴ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የሩዝ ልማት ስራው አርሶ አደሩ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ ከማድረግ ባሻገር ለገበያ የሚቀርብ ምርት እንዲኖረው አድርጓል። በተያዘው ክረምትም በፎገራ ፣ ሊቦከምከምና ደራ ወረዳዎች 107 ሺህ ሄክታር መሬት በሩዝ ሰብል ለመሸፈን ታቅዶ እስከ አሁን በተደረገው ጥረት 91 በመቶውን ለማሳካት ተችሏል ነው ያሉት። አርሶ አደሩ ቴክኖሎጂንና ግብአትን በአግባቡ በመጠቀም በሩዝ ልማት ስራው ምርታማነቱን እንዲያሳድግም የባለሙያዎች ድጋፍና ክትትል እየተደረገለት መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ባለፈው ዓመት የመኸር ወቅት በሄክታር በአማካይ የተገኝውን 56 ኩንታል የሩዝ ምርት በዘንድሮው ዓመትም ወደ 65 ኩንታል ለማሳደግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ያስችላል ብለዋል። አሁን ላይ የሩዝ ልማት ከመስፋፋቱና ምርታማነቱ ከማደጉ ጋር ተያይዞ አርሶ አደሩ ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለሀገር ውስጥ ገበያ የማቅረብ አቅም መገንባቱን አስረድተዋል። ከአካባቢው የአየር ንብረት ሁኔታ ጋር የተቀናጀው የሩዝ አመራረት ሂደት፣ የምግብ ዋስትና በአስተማማኝ ሁኔታ ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት ከማገዝ ባለፈ አርሶ አደሩ ለገበያ የሚተርፍ ምርት እንዲያገኝ አድርጓል ብለዋል። በወረታ ከተማ አስተዳደር የወረታ ዙሪያ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር አብራራው ጀግኔ፤ በሩዝ ልማት ስራ ምርታማነታቸውን በማሳደግ ሃብት ለመፍጠር እንደቻሉ ነው የሚናገሩት። በዘንድሮው ዓመትም በአንድ ሔክታር መሬት ላይ የተሻሻሉ የሩዝ ዘርና ግብአት ተጠቅመው በመዝራት የተሻለ ምርት ለማግኝት እየሰሩ መሆኑን አመልክተዋል። ሌላው የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ዳኛው አልጣህ በበኩላቸው፤የነበራቸው መሬት ውኃ የሚተኛበት በመሆኑ ከሚዘሩት ጤፍና ኑግ በቂ የሆነ ምርት ስለማይገኝ ለተረጂነት ተጋልጠው እንደቆዩ ነው የሚናገሩት። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን ተግባራዊ የተደረገው የሩዝ ልማት ስራ ውሃማ አካባቢን የሚፈልግ በመሆኑ ምርታማ በመሆን ሃብት ለመፍጠር መቻላቸውን ነው የገለጹት። ገለባውንና ተረፈ ምርቱንም በመኖነት በመጠቀም ከብት በማደለብ እና በወተት ልማት በመሰማራት በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የሚገልጹት።
የኢንዱስትሪ ምርቶች ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትና ለውጭ ገበያ የማቅረብ አቅም እያደገ መጥቷል-ሚኒስትር መላኩ አለበል
Jul 29, 2026 203
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 22/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርቶች ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የማሳደግና እና ለውጭ ገበያ የማቅረብ አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ። ኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማ እና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ መድረክ አካሂዷል። በተጨማሪም ሚኒስቴሩ በበጀት ዓመቱ ወደ ውጭ የመላክ የላቀ አፈጻጸም ላሳዩ አምራች ኢንዱስትሪዎች የእውቅና እና የምስጋና መርሃ ግብር አካሂዷል። ሚኒስትር መላኩ አለበል በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ በሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ የላቀ ሚና አበርክቷል። በአምራች ዘርፉ የሚመሩ የተለያዩ ስትራቴጂዎችን በመቅረጽ ዘርፉን የማነቃቃትና የመደገፍ ሥራ መሠራቱንም ጠቁመዋል። የኢንዱስትሪ ካውንስል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አማካኝነት ተቋቁሞ፣ የኢንዱስትሪዎችን ችግር ከመለየት ጀምሮ በዘላቂነት ተወዳዳሪ ሊሆኑ የሚችሉበትን አሰራር መዘርጋቱን ገልጸዋል። በዚህም በዘርፉ የነበሩ ማነቆዎች ለይቶ መፍትሔ በመስጠት ምርት እና ምርታማነት በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪ ችግሮች እንዲፈታ ታስቦ ተግባራዊ መሆን ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በዘርፉ ከፍተኛ ውጤቶች መመዝገባቸውን አመላክተዋል። ይህ ንቅናቄ ሥራ አቁመው የነበሩ በርካታ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ እንዲመለሱ ማድረጉን እና አዳዲስ ኢንቨስትመንቶችም እንዲሰማሩ ማስቻሉን ተናግረዋል። በዚህም ገቢ ምርቶችን በመተካት እና የወጭ ንግድን በማሳደግ ረገድ የማይተካ ሚና ማበርከቱን ጠቁመዋል። የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የፋይናንስ ማነቆ ለመፍታት በተወሰደ እርምጃ፣ ቀደም ሲል 40 ቢሊዮን ብር የነበረውን የብድር መጠን ወደ 115 ቢሊዮን ብር ከፍ ማድረግ ተችሏል። "ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ በተጀመረበት ወቅት ለአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ ይቀርብ የነበረው የውጭ ምንዛሬ መጠን አሁን ላይ ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ማድረስ መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም የኢንዱስትሪዎቻችን ተወዳዳሪነት፣ ምርታማነት፣ ትርፋማነት እና የመስፋፋት ዕድል ከፍ እያለ መምጣቱን ገልጸዋል። ከ2014 በፊት ኢንዱስትሪዎች ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በመተካት ረገድ ከ348 ሚሊዮን ዶላር በላይ የሚያድኑ አልነበሩም ያሉት ሚኒስትሩ፣ አሁን ላይ ግን 5 ነጥብ 9 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን ተናግረዋል። ይህም የንግድ ሚዛንን በማጣጣሙ በኩል የኢትዮጵያን ዘላቂ ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ ከፍተኛ ድርሻ ማበርከቱን አብራርተዋል። በወጭ ንግድ በኩል ቀደም ሲል ይገኝ የነበረው 385 ሚሊዮን ዶላር በዚህ ዓመት ወደ 607 ሚሊዮን ዶላር ማደጉን ጠቁመው፤ የአምራች ዘርፉ ለሥራ ዕድል ፈጠራም ትልቅ አማራጭ እየሆነ መምጣቱን ጠቁመዋል። በ2019 በጀት ዓመት ከወጭ ንግድ የሚገኘውን ገቢ ወደ 1 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን ገልጸው፣ ይህንን ዕቅድ ለማሳካት ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እንደሚሠራም አረጋግጠዋል። በእውቅናና ምስጋና መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት አምራቾች በበኩላቸው፤ በኢንዱስትሪው ዘርፍ የተደረጉ የፖሊሲ ማሻሻያዎችና አዳዲስ አቅጣጫዎች ለዘርፉ አዎንታዊ ሚና ማበርከታቸውን ገልጸዋል፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል አቶ ሀብታሙ ዳርጌ፤ የተደረጉት የፖሊሲ ማሻሻያዎች የሪፎርም ስራዎች ለአምራቾች ትልቅ ዕድል ይዞ መምጣቱን ጠቅሰዋል፡፡ ማሻሻያዎቹ የምርት መጠናቸውንና ምርታማነታቸውን በከፍተኛ ደረጃ እንዳሳደገላቸው የገለጹት ደግሞ ህይወት ዳመኑ ናቸው።
በምስራቅ ሸዋ ዞን በመኸር ወቅት እርሻ ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል
Jul 29, 2026 220
አዳማ፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ)፦በምስራቅ ሸዋ ዞን በመኸር ወቅት እርሻው ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት መታቀዱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለፀ። የምስራቅ ሸዋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን ከ20 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ታቅዶ እየተሰራ ነው። በዞኑ በዘንድሮው የመኸር ወቅት ለማልማት ታቅዶ ከነበረው ከ530 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ውስጥ እስካሁን ከ475 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በተለያየ ምርጥ ዘር መሸፈኑን ተናግረዋል። ለዚህም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል የአፈር መዳበሪያ ለማቅረብ መታቀዱን ጠቅሰው፣ እስካሁን ከ800 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ መቅረቡን ገልጸዋል። የታቀደውን ምርት ለማግኘትም የግብርና ቴክኖሎጂ፣ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ በስፋት ጥቅም ላይ መዋሉን ጠቅሰው፤ለአርሶ አደሩም ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ነው ብለዋል። የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የግብርና ምርቶችን የኤክስፖርት አቅም ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት ለመደገፍ በዕቅድ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የኤክስፖርት ምርቶችን ለመጨመር በስንዴ፣በቦሎቄና በሽንብራ ላይ በሜካናይዜሽን የተደገፈ የኩታ ገጠም የሰብል ልማት እየተከናወነ መሆኑንም አክለዋል። የዞኑን ግብርና ከበሬ ማረስ በማውጣት ወደ ሜካናይዜሽን ለማሸጋገር በተያዘው ዓመት 155 የእርሻ ትራክተሮች ተገዝተው በልማት ስራ ላይ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በዞኑ ስንዴ፣ ቦሎቄ፣ ሽንብራ፣ ጤፍና ሌሎች ዋና ዋና ሰብሎች በ460 ክላስተር በመደራጀት እየለሙ መሆናቸውን ምክትል ኃላፊው አስረድተዋል።
በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ93 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰብስቧል
Jul 28, 2026 410
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 21/2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ93 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ እንደተቻለ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ። የባህር ዳር ከተማ ገቢዎች መምሪያ "ግብሬን ደስ ብሎኝ እከፍላለሁ" በሚል መሪ ቃል የ2018 አፈፃፀም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት እቅድ ትውውቅ መድረክ አካሂዷል። የቢሮ ኃላፊው መንገሻ ፈንታው(ዶ/ር) እንደገለጹት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ93 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ ስኬታማ ስራዎችን አከናውኗል ። ቢሮው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ100 ነጥብ ሶስት ቢሊዮን በላይ ለመሰብሰብ አቅዶ ሲሰራ የቆየ ሲሆን የእቅዱን 92 በመቶ ማሳካት መቻሉን ገልጸዋል። የተሰበሰበው ገቢ ለክልሉ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እድገት በማዋል በራስ የመልማት አቅም ለመገንባት የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ነው የተናገሩት። ቢሮው ከባህዳር ዩኒቨርሲቲና ከኢትዮ-ቴሌኮም ኩባንያ ጋር በመተባበር በዲጂታል ግብር የመክፈል ስርአት መዘርጋቱ ለዘርፉ ውጤታማነት አስተዋጽኦ ማበረከቱን አስረድተዋል። ይህም ደንበኞች ባሉበት ቦታ ሆነው ግብር በመክፈል ፈጣን፣ ተአማኒነት ያለውና ፍትሃዊ አገልግሎት እንዲያገኙ በማድረግ የመልካም አስተዳደር ችግርን ለመቅረፍ የሚያስችል መሆኑን አስገንዝበዋል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ኃይለማርያም እሸቴ በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ዘጠኝ ቢሊዮን ብር ገቢ በመሰብሰብ የዕቅዱን 91 በመቶ ማሳካት ተችሏል ብለዋል። በተሰበሰበው ገቢም በከተማዋ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች የልማት ስራዎችን በማከናወን የህዝቡን የመልማት ጥያቄ ለመመለስ የሚውል እንደሆነም አስረድተዋል። በ2019 በጀት ዓመትም የግብር አሰባሰብ ስርአቱን ይበልጥ ግልጽ፣ ፍትሐዊና በህዝብ ዘንድ ተአማኒነት ያለው ለማድረግ በተሻለ መንገድ እንደሚሰራ አስገንዝበዋል። በመድረኩ ማጠናቀቂያ ላይም ለምስጉን ግብር ከፋዮችና ከፍተኛ ገቢ ለሰበሰቡ ተቋማት እውቅና የመስጠት ስነ ስርአት ተካሂዷል።
በሰሜን ሸዋ ዞን ከ177ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈን ተችሏል
Jul 28, 2026 232
ደብረ ብርሃን፤ ሐምሌ 21/ 2018(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን በተያዘው ክረምት ከ177 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈን መቻሉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በዞኑ ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ባለሙያ ወይዘሮ ሁሉምታየ ዘነበ እንደገለፁት፤ በዚህም በ2018/19 የመኸር ምርት ዘመን 563 ሺህ 336 ሄክታር መሬት በሰብል ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል። ባጠቃላይ ከሚለማው ማሳ ውስጥም ከ308 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነውን በኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴ በመጠቀም በጤፍ ፣ ስንዴ ፣ ማሽላ፣ በቄላና ማሾ ሰብሎች ለማልማት እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። አስካሁን በተደረገው ጥረትም 196 ሺህ 417 አርሶ አደሮችን በማሳተፍ177 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር መሸፈን መቻሉን ገልጸዋል። የዘርፉ አመራርና ባለሙያዎችም አርሶ አደሩ የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴን፣ሌሎች የተሻሻሉ አሰራሮችንና ግብአትን ተጠቅመው በመዝራት ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ ድጋፍ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። በተጨማሪም ዝናቡ ዘግይቶ በጣለባቸው አካባቢዎች ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን እንዲዘራና በማሳው ዳር እና ዳር ውሃን አቅቦ የሚያቆይ ጉድጓድ በመቆፈር እንዲጠቀም ጥረት እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል። በዞኑ የሞረትና ጅሩ ወረዳ አርሶ አደር የሆኑት መዝገቡ ወልዴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ስድስት ሄክታር መሬታቸውን በኩታ ገጠም በማረስ በስንዴ፣በጤፍና በጥራጥሬ ሰብሎች ሸፍነዋል። በአሁኑ ወቅትም ቡቃያውን መንከባከብ መጀመራቸውን ነው የተናገሩት። ሌላው የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ማሙሽ በቀለ በበኩላቸው፤ያለው የዝናብ ስርጭት ጥሩ በመሆኑ ሶስት ሄክታር መሬታቸውን በሰንዴ ሰብል መሸፈን መቻላቸውን አስረድተዋል። ምርታማነታቸውን ለማሳደግም የሚያስፈልጋቸውን ማዳበሪያና ምርጥ ዘርን በወቅቱ ማግኘት በመቻላቸው ፈጥነው ወደ ዘር ስራ መግባታቸውን ተናግረዋል። በዞኑ ከመኸር እርሻ 20 ነጥብ ስምንት ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማምረት ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በክልሉ የቡና ምርታማነትን በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ከፍ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 28, 2026 258
ሚዛን አማን፣ ሐምሌ 21/2018 (ኢዜአ):- በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የቡና ልማትን በማስፋፋትና ምርታማነትን በማሳደግ ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ከፍ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ባለሥልጣን ገለጸ። የባለሥልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ በላይ ኮጁአብ ለኢዜአ እንዳሉት በክልሉ ከቡና የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ከፍ ለማድረግ ልማቱን የማስፋፋትና ምርታማነትን ማሳደግ ላይ ትኩረት ተሰጥቷል። በዚህም በክረምቱ ወራት ከ25 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኞችን ለመትከል ወደስራ መገባቱን ተናግረዋል። የቡና ልማቱን ለማሳካት ዝርያቸው የተሻሻሉና ለደጋና ቆላማ አየር ንብረት ተስማሚነታቸው በምርምር የተረጋገጡ ችግኞች ለአርሶ አደሩ መሰራጨታቸውን ጠቁመዋል። የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችም በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ለምርት የሚደርሱ እና ከነባሩ የቡና ዝርያ በእጥፍ ምርት የሚሰጡ መሆናቸውን ጠቅሰው ልማቱን ለማሳካትም ሙያዊ ድጋፋና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በሸካ ዞን የየኪ ወረዳ አርሶ አደር ሰሎሞን ብርሃኔ ከቡና የሚያገኙትን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ያላቸውን የቡና ማሳ በየዓመቱ እያስፋፉ መሆኑን ገልጸዋል። አምና ከወረዳው ያገኙትን አንድ ሺህ "ኬ1" የተሰኘ ምርጥ የቡና ችግኝ መትከላቸውንና ዘንድሮም ተግባሩን በማስቀጠል አንድ ሺህ ችግኞችን ለመትከል እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ነባሩን የቡና ዝርያ በምርምር በተገኙ የቡና ዝርያዎች እየተኩ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ አርሶ አደር ጢሞቴዎስ ከሮ እና ታደሰ እጅጉ ናቸው። ቡናን ከማልማት ባሻገር ጥራቱን ለማስጠበቅ በግብርና ባለሙያ ትምህርት ታግዘው እየሠሩ መሆናቸውን አመልክተዋል። ያላቸው ማሳ ላይ በየዓመቱ አዳዲስ ችግኞችን እየተከሉ የቡና ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ትኩረት መስጠታቸውን ገልጸዋል። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል 614 ሺህ ሄክታር መሬት በቡና እየለማ መሆኑ ታውቋል።
ዘመናዊ የመሬት አያያዝ እና አስተዳደር ለጠንካራ ኢኮኖሚ ግንባታ ሚናውን እየተወጣ ነው
Jul 28, 2026 187
ጅማ ፤ሐምሌ 21/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት በሚከናወኑ ተግባራት ዘመናዊ የመሬት አያያዝ እና አስተዳደር አገልግሎት ትልቅ ሚና እየተጫወተ መሆኑ ተገለጸ። በጅማ ከተማ በዛሬዉ ዕለት የገጠር ካዳስተር ስፍር የመዝጊያ ፕሮግራም ተካሂዷል። በመዝጊያ ፕሮግራሙ ላይ በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሀላፊ ነመራ ቡሊ ፣ የኦሮሚያ መሬት ቢሮ ሀላፊ መሠረት አሰፋ እና ሌሎችም የዞን እና የወረዳ የስራ ሀላፊዎች ተገኝተዋል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሀላፊ ነመራ ቡሊ በወቅቱ እንደገለጹት ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት በሚከናወኑ ተግባራት ውስጥ የመሬት አስተዳደር ትልቅ ሚና አለው። ይህንን ከግብ ለማድረስ በቴክኖሎጂ የታገዘ ዘመናዊ የመሬት አስተዳደር አገልግሎት ተግባራዊ እየተደረገ ነው ብለዋል። በክልሉ የተሰራው የካዳስተር ስራም ተጨባጭ ለዉጥ ማምጣቱን ጠቅሰዋል። ዘመናዊ የመሬት አያያዝ እና አስተዳደር አገልግሎትን በማሳካት ወደ ትልቅ የገቢ ምንጭ የመቀየር ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው ተግባሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል ። የኦሮሚያ መሬት ቢሮ ሀላፊ መሠረት አሰፋ በበኩላቸዉ የመሬት ካዳስተር አገልግሎት ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን አስገኝቷል ብለዋል። ከዚህ ውስጥ አርሶ አደሮችን ወደ ኢንቨስትመንት ማሸጋገር ፣ የመሬት ብክነትን ማስቀረትና ግልፅና ቀልጣፋ አገልግሎትን መስጠት እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል ። በክልሉ በ21 ዞኖች ለ4 ሚሊዮን 69 ሺህ 179 አርሶ አደሮች የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ መሰጠቱን አስታውቀዋል። የጅማ ዞን አስተዳዳሪ ቲጃኒ ናስር በበኩላቸው የካዳስተር አገልግሎት የዞኑን ገቢ ከማሳደግ በተጨማሪ ኢንቨስትመንትን እያጠናከረ ነዉ ብለዋል። ግልፅነትን በማስፈን ሀብትን በአግባቡ መጠቀም ያስቻለ መሆኑንም አመልክተዋል። የጅማ ዞን መሬት ፅህፈት ቤት ሀላፊ አብዱልሀሚድ ሀጂ በዞኑ የተጀመረዉ የመሬት ካዳስተር አገልግሎት በርካታ ጠቀሜታ ማስገኘቱን ጠቁመው በ20 ወረዳዎች እና በ513 ቀበሌዎች መሬት በካዳስተር መሰፈሩን ተናግረዋል። በዚህም ለ397 ሺህ 647 አርሶ አደሮች የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ መሰጠቱን ገልፀዋል። የካዳስተር አገልግሎት የአርሶ አደሩን የመሬት አጠቃቀምና አስተዳደር በማሻሻል ግንዛቤን ማሳደጉንም አክለዋል። በጅማ ዞን የሰኮሩ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ዝናብ አባ ጎጀም ሁለት ሄክታር መሬታቸዉ ተሰፍሮ የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ማግኘታቸዉን ተናግረዉ አገልግሎቱ መሬታቸውን በአግባቡ ለማስተዳደር እንዳገዛቸዉ ጠቅሰዋል። ሌላዉ የሊሙ ሰቃ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ፋሪስ መሀሙድ መሬት ወደ ካዳስተር መግባቱ ከዚህ ቀደም በአካባቢያቸዉ በባለቤትነት ዙሪያ ይነሱ የነበሩ ቅሬታዎችን መፍታቱን ገልፀዉ የይዞታ ማረጋገጫ በማግኘቴ ተደስቻለሁ ብለዋል።
በጉራጌ ዞን በፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ነው
Jul 28, 2026 258
ወልቂጤ ፤ሐምሌ 21/2018(ኢዜአ)፦ በፍራፍሬ እና ቅመማ ቅመም ልማት ላይ መሰማራታችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን ለማሳደግ አስችሎናል ሲሉ የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች ተናገሩ። ኢዜአ ያነጋገራቸው በዞኑ የአበሽጌ እና የቸሃ ወረዳ አርሶ አደሮች፤ከእንሰት እና ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በፍራፍሬ እና ቅመማ ቅመም ልማት ላይ በመሰማራት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ገልጸዋል፡፡ የአበሽጌ ወረዳ አርሶ አደር ዳዊት አሰፋ ፤ በግብርና ባለሙያዎች በተደረገላቸው ድጋፍ ሁለት ሄክታር መሬታቸው ላይ ቅመማ ቅመም ማምረት መጀመራቸውን ገልፀዋል። በአካባቢው ከእንሰት እና ሰብል ልማት ባለፈ የቅመማ ቅመም ልማት ብዙም ያልተለመደ እንደነበር ጠቅሰው አሁን ላይ በፍራፍሬ ልማት ላይ በመሳተፍም ገቢያቸውን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። ሌላው የወረዳው አርሶ አደር ሞሳ ጀማል፤ላለፉት አራት አመታት የተለያዩ የፍራፍሬ እና ቅመማ ቅመምን በማምረት ለገበያ አቅርበው ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የገለጹት፡፡ የተሰማሩበትን የፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ልማት ስራ ውጤታማ ለማድረግም በዘርፉ ውጤታማ የሆኑ አርሶ አደሮችን ልምድ ከመውሰድ ባለፈ የባለሙያዎች ድጋፍንም ተግባራዊ ማድረጋቸውን ጠቁመዋል። በፍራፍሬ እና በአትክልት ልማት ላይ በመሰማራት በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ገቢያቸውን ማሳደጋቸውን የተናገሩት ደግሞ የቸሃ ወረዳ አርሶ አደር ዲሮ በድር ናቸው፡፡ የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ እንደገለጹት ፤ በዞኑ የፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ውጤታማ ናቸው። በተለይ በአቮካዶ፣ ሙዝ፣ ማንጎ ፣ አናናስ እና ፓፓያ ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉን ገልፀዋል። በዞኑ ፍራፍሬና አትክልትን በስፋት ከማልማት በተጨማሪ በቅመማ ቅመም ልማት ላይ በማተኮር ከፍተኛ ውጤት እየተመዘገበ ነው ብለዋል። በዘንድሮ አመት 2 ነጥብ 5 ሚሊዮን የተሻሻሉ የአቮካዶ፤ የፓፓያ እና የተለያዩ ፍራፍሬ ችግኞች መሰራጨታቸውን ተናግረዋል። ልማቱን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግም ለአርሶ አደሩ ከማሳ ዝግጅት እስከ ምርት አሰባሰብ የባለሙያዎች ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
አፍሪካ የራሷን ዘላቂና አስተማማኝ የፋይናንስ ምንጭ በመገንባት ዓለም አቀፍ ተደማጭነቷን ማጎልበት አለባት
Jul 28, 2026 182
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 21/2018(ኢዜአ)፦ አፍሪካ የራሷን ዘላቂና አስተማማኝ የፋይናንስ ምንጭ በመገንባት ዓለም አቀፋዊ ተደማጭነቷንና ተጽዕኖ ፈጣሪነቷን ማጎልበት እንዳለባት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ገለጹ። 49ኛው የአፍሪካ ሕብረት የሥራ አስፈጻሚዎች ምክር ቤት ስብሰባ "የአፍሪካ አጀንዳ 2063ን ለማሳካት ዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ሥርዓት ማንበር" በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ ይገኛል። የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የጂኦፖለቲካ ውድድር፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖዎች በዓለም አቀፍ ሥርዓት ላይ ለውጥ እያመጡ ነው። አፍሪካ የዓለምን ተለዋዋጭና ኢ-ተገማች ሁኔታ እንደ መልካም አጋጣሚ በመውሰድ ሁነቱን በራሷ መንገድ መቅረጽ እንዳለባትም ገልጸዋል። ለዚህም አህጉራዊ ተቋማት የዓለምን ነባራዊ ሁኔታ ታሳቢ ያደረጉ ሪፎርሞችን ማድረግ እንዳባቸው ነው የተናገሩት። ሕብረቱም በቴክኒካዊና ጥቂት ማስተካከያዎች ላይ ብቻ ሳይወሰን ስትራቴጂክና ፖለቲካዊ ውሳኔዎችን ያካተተ ጥልቅ ማሻሻያ ማድረግ እንደሚኖርበት አስገንዝበዋል። አፍሪካ ዓለም አቀፋዊ ተደማጭነቷንና ተጽዕኖ ፈጣሪነቷን ለማሳደግ የራሷን ዘላቂና አስተማማኝ የፋይናንስ ምንጭ ሊኖራት ይገባል ብለዋል። በዚህም አፍሪካ ለዓለም አቀፍ ችግሮች አህጉራዊ መፍትሔን በማበጀት ቁልፍ ተዋናይ መሆን እንደሚጠበቅባት ገልጸዋል። አፍሪካ በሚያጋጥሟት ፈተናዎች መሀል ዕድገት እያስመዘገበች ነው ያሉት ሚኒስትሩ፤ በ2026 ፈጣን ዕድገት ከሚያስመዘግቡ 10 የዓለም ሀገራት መካከል ስምንቱ አፍሪካውያን እንደሚሆኑ ይጠበቃል ብለዋል። የአፍሪካ ሕብረት በዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ ተጽዕኖ ለማሳደር ውሳኔዎቹን ማስፈጸም የሚያስችለውን ሪፎርም በማድረግ ዘላቂና አስተማማኝ የፋይናንስ ምንጭ ሊኖረው እንደሚገባ ነው ያመለከቱት። የአፍሪካ ሃብቶች በአህጉሪቱ ተቋማትና ማዕቀፎች መመራት እንዳለባቸው ጠቁመው፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረትን የአህጉራዊ አንድነትና የጋራ ራዕይ ዋነኛ ተቋም አድርጋ ትመለከታለች ብለዋል። ለሕብረቱ ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎችና ዘላቂ ግቦች መሳካት በትኩረት እንደምትሰራም አስገንዝበዋል። የሕብረቱ የሥራ አስፈጻሚዎች ምክር ቤት በአፍሪካ ሕብረት የ2026 የዓመቱ መሪ ሀሳብ ትግበራና አፈጻጸም ላይ በቀረበው ሪፖርት ላይ በጥልቀት ይመክራል። በተጨማሪም የአፍሪካ ሕብረት ስምምነቶች በፍጥነት በሚጸድቁበትና በሚተገበሩባቸው ጉዳዮች እንዲሁም በአጀንዳ 2063 ትግበራ ዙሪያ በቀረበው የኮሚቴው ሪፖርት ላይ ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል።
ግብርን በአግባቡና በወቅቱ በመክፈል የሚጠበቅብንን ሀገራዊ ግዴታ እየተወጣን ነው
Jul 28, 2026 114
ሀረር ፤ሐምሌ 21/2018(ኢዜአ)፦ ግብርን በአግባቡና በወቅቱ በመክፈል ሀገራዊ ግዴታቸውን እየተወጡ መሆኑን የሐረሪ ክልል ግብር ከፋዮች ተናገሩ። የሐረሪ ክልል ታማኝ ለሆኑና ግብራቸውን በወቅቱ በመክፈል ላይ ላሉ ነጋዴዎች እውቅና ሰጥቷል። ኢዜአ ያነጋገራቸው ግብር ከፋዮች እንዳሉት ግብርን በአግባቡና በወቅቱ በመክፈል የሚጠበቅባቸውን ሀገራዊ ግዴታ እየተወጡ ነው። ከክልሉ ታማኝ ግብር ከፋዮች መካከል በአይን ህክምና ስራ ላይ የተሰማሩት ዶክተር ኑረዲን አብዲ እንዳሉት፤ የሚጠበቅብኝን ግብር በወቅቱ በመክፈሌ የተሰጠኝ እውቅና ለበለጠ ስራ የሚያነሳሳ ነው። ከነጋዴው የሚሰበሰበው ግብር ለአካባቢው ልማት መፋጠን የሚውል በመሆኑም ስራዎችን በማሳደግ ለሀገር እድገት ይበልጥ አስተዋጽኦ ለማድረግ እንደሚሰሩ ነው የገለጹት። ግብርን በአግባቡ መክፈል ለመጪው ትውልድ ምቹ የሆነች ሀገር ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ውስጥም የራስን አሻራ ለማኖር የማያስችል ነው ብለዋል። በከተማው በሆቴል ስራ የተሰማሩት አቶ ሃይሉ ካሳ እና ወይዘሮ ዩስራ መሀመድ በበኩላቸው፤ ግብር መክፈል ለሀገር ልማትና እድገት የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ በመገንዘብ የዜግነት ግዴታችን በመወጣት ላይ ነን ብለዋል። በተለይም'' በአሁኑ ወቅት በሚካሔዱ የልማት ስራዎች ተጠቃሚ በመሆናችን በወቅቱ በተገቢው መንገድ ወደንና ፈቅደን በሚፈለገው መንገድ ግብራችንን መክፈልን እንቀጥላለን'' ነው ያሉት። በክልሉ መንግስት የተሰጣቸው እውቅናም ይበልጥ ለመስራትና ለሌሎች አርአያ ለመሆን እንዳነሳሳቸው አመልክተዋል፡፡ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ ያሲን አብዱላሂ እንደገለጹት፤ በክልሉ በፍቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የታክስ ተገዢነትን በማሳደግ የክልሉን የልማት ወጪ በራስ ገቢ ለመሸፈን በማቀድ ወደ ስራ ተገብቷል። በተለይ የታክስ ህጎችን ወደ ስራ በማስገባት ፍትሃዊ የግብር ክፍያዎች እየተፈጸሙ መሆኑን የገለጹ ሲሆን ይህም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገና ለውጥ እየተመዘገበበት እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዘንድሮ በጀት ዓመት በክልሉ ከተለያዩ የገቢ ርዕሶች ከ6 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን አመልክተዋል። በቀጣይም የታክስ አሰባሰብ ስርዓቱን የማዘመን እና የንግዱ ማሕበረሰብ በታክስ አሰባሰቡ ሒደት ላይ ግንዛቤውን የማስፋት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል።
በክልሉ የመጠባበቂያ እህል ክምችትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jul 28, 2026 108
ሀዋሳ ፤ሐምሌ 21/2018(ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል የሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን ለመቋቋም የሚያስችል የመጠባበቂያ እህል ክምችትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ አደጋ ስጋት አመራርና ድጋፍ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ገለጸ። ከ300 ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይም ለዚሁ ተግባር የሚውል የበቆሎ ልማት እየተከናወነ መሆኑ ተመላክቷል። የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ኃይሉ ሀሰና እንደገለጹት፤ በክልሉ የሚያጋጥሙ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመመከት የሚያስችል አቅም ለመገንባት እየተሰራ ነው። በክልሉ አምስት ወረዳዎች ውስጥ የወል መሬትን በመጠቀም በቆሎ፣ ቦሎቄና ሌሎች ሰብሎችን በማምረት የመጠባበቂያ እህል ክምችት አቅምን የማሳደግ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም ከ300 ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ በቆሎ እየለማ እንደሚገኝ ጠቅሰው ከ12 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ይሰበሰባል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ ህብረተሰቡ በ"ካላሞ ፎጮ" ስርዓት እርስ በእርሱ የሚረዳዳበትን ባህል የማጎልበት ተግባር እየተከናወነ ነው ብለዋል። ይህም አርሶ አደሩ እህል በሚሰበሰብበት ጊዜ ከሚያገኘው ምርት ለወገኖቹ እንዲያጋራ በማድረግ የገንዘብ፣ የአልባሳትና የቁሳቁስ ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በተጨማሪም በዝናብ መስተጓጎል ምክንያት ማሳቸው የተጎዳባቸው አርሶ አደሮች የማካካሻ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ እንዲደርሳቸው መደረጉንም አክለዋል። በክልሉ የደራራ ወረዳ አርሶ አደር በላይ ግዴሳ፤ በሁለት ሄክታር ማሳ ላይ ካለሙት የበቆሎ ምርት ላይ በባህላዊ የመረዳጃ ስርዓቱ "ካላሞ ፎጮ" መሰረት እስከ አምስት ኪሎ ግራም ረዳት ለሌላቸው ወገኖች እንደሚለግሱ ገልጸዋል። የሀዋሳ ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አለማየሁ ዲጋ በበኩላቸው፤ ከሚያገኙት የበቆሎ ምርት ላይ እስከ አምስት ኪሎ ግራም ለተቸገሩ ወገኖች መርጃ እንዲሆን በ"ካላሞ ፎጮ" በኩል እንደሚለግሱም ተናግረዋል።