ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ከአረንጓዴ አሻራ እስከ ዓለም ገበያ - የኢትዮጵያ ቡና ልማት አዲስ የዕድገት ምዕራፍ
Aug 13, 2026 99
(በሙሴ መለሰ) ኢትዮጵያ የቡና መገኛ ከመሆኗም ባለፈ ምርቱ አሁንም ለሀገሪቱ ምጣኔ ሀብትና ማህበራዊ ህይወት ትልቅ መሰረት ያለው ነው። የዓለም የቡና ዝርያዎች ሁሉ መገኛ የሆነው የአረቢካ ቡና ለመጀመሪያ ጊዜ የተገኘውም በኢትዮጵያ እንደሆነ ይታወቃል። በኢትዮጵያ ቡና መጠጣት የዕለት ተዕለት ባህል ሲሆን፣ የቡና አፈላል ስነ ስርዓት ሰላምን፣ አንድነትንና ማህበራዊ ውይይትን የሚያጠናክር ትልቅ እሴት ተደርጎም ይወሰዳል። በአሁኑ ወቅት ቡና ለሀገሪቱ ከፍተኛውን የውጭ ምንዛሬ ገቢ የሚያስገኝ ቀዳሚው የግብርና ምርት በመሆን ማዕከላዊ የኢኮኖሚ ሚናውን እየተጫወተ ይገኛል። አብዛኛው የኢትዮጵያ ቡና የሚመረተው በተፈጥሯዊ መንገድ በገበሬዎች ማሳ ላይ ወይም በዱር ውስጥ በመሆኑ፣ ለሰው ሰራሽ ማዳበሪያና ኬሚካል ተጋላጭ አይደለም። ይህም በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለውን ተመራጭነት ይበልጥ ከፍ አድርጎታል። ከኢትዮጵያ የወጪ ንግድ ምሰሶ አንዱ የሆነው ቡናችን ለሀገሪቷ እያስገኘ ያለው ገቢም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከምክር ቤቱ ለተነሱላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ማብራሪያ ካነሷቸው ጉዳዮች መካከልም አንዱ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዋልታ የሆነው ቡና ነበር። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከብራዚልና ኮሎምቢያ በመቀጠል በዓለም 3ኛዋ ትልቋ የቡና ላኪ ሀገር መሆኗን እና በአፍሪካም ቀዳሚ ደረጃ ላይ መቀመጧን ገልጸዋል። በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ከቡና ወጪ ንግድ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ የተገኘ ሲሆን፣ ይህ ውጤት ባለፉት 17 ዓመታት በድምሩ ከተገኘው 3 ነጥብ3 ቢሊዮን ዶላር ጋር ሲነጻጸር በዘርፉ የተመዘገበውን ከፍተኛ ዕድገት ያሳያል ብለዋል። ለተመዘገበው ውጤት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱ የተጠቀሰ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን እምቅ አቅም አጠናክራ መጠቀም እንዳለባት ተናግረዋል። የግብርና ሚኒስትሩ አዲሱ አረጋ የኢትዮጵያን የቡና ዘርፍ ከዘልማዳዊ አሰራር ወደ ዘመናዊ ምርታማነት ለማሸጋገር የሚያስችል አዲስ የ10 ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ እና የተሻሻለ የልማት ፓኬጅ መዘጋጀቱን በቅርቡ ባስተላለፉት መልዕክት ገልጸዋል። ቡና በሀገሪቱ ኢኮኖሚ፣ የሚሊዮን አርሶ አደሮች የኑሮ መሠረትና የወጪ ንግድ ዋነኛ ምሰሶ መሆኑን ጠቅሰው ይህንን ታላቅ ሀብት በጥራትና በዘላቂነት በማሳደግ ከምርት ወደ እሴት፣ ከእሴት ወደ ዓለም ገበያ ማሸጋገር የዘርፉ ዋነኛ አቅጣጫ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንኑ ስትራቴጂ ለማሳካት የተጀመረው ሃገራዊ የቡና ምርትና ምርታማነት ኢኒሼቲቭ በአሁኑ ወቅት በሔክታር 9 ኩንታል የሆነውን የቡና ምርታማነት ወደ 21 ኩንታል ለማሳደግ ያለመ መሆኑን ሚኒስትሩ አብራርተዋል። በተጨማሪም በ 1 ነጥብ15 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ላይ የቡና ልማት ለማካሄድ የታቀደ ሲሆን፣ ለዚህም ምርጥ የቡና ዘር አጠቃቀም፣ የተቀናጀ የአፈር ንጥረ-ነገር፣ የቡና ተክል ጥግግት፣ የገረዛና የጥላ ዛፍ አያያዝ፣ የተቀናጀ የተባይ መከላከል፣ የመስኖ፣ የማዳበሪያ እንዲሁም የተሻሻለ የምርት አሰባሰብና የዕድሳት ሥራዎችን ያካተቱ ዘጠኝ የትኩረት መስኮች ተለይተው ወደ ሥራ መግባታቸውን አመልክተዋል። ይህ አዲሱ የቡና ልማት ኢኒሼቲቭ አርሶ አደሮችን፣ የማህበራትንና የባለሙያዎችን ግንዛቤና አቅም ለማሳደግ ሰፊ የንቅናቄ ሥራዎችን እንደሚከናውን ሚኒስትሩ ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በቡና ወጪ ንግድ ከአፍሪካ ቀዳሚና ከዓለም 3ኛዋ ትልቅ ላኪ ሀገር በመሆን ያሳየችው እመርታ፣ የዘርፉን ታላቅ የምጣኔ-ሀብት አቅም በተጨባጭ የሚያሳይ ነው። ለዚህ ደግሞ ላለፉት ዓመታት የተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የተፈጥሮን ምህዳር በማስተካከል ረገድ የራሱን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱ ይታወቃል። በዚህም መርሃ-ግብሩ በተጀመረበት 2011 ዓ.ም 600 ሺህ ሔክታር መሬት ላይ የተተከለው የቡና ችግኝ በየዓመቱ እያደገ በመሔድ በ2017 ዓ.ም ላይ 1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር መሸፈን ተችሏል። ይሄ በመሆኑም የቡና ምርታማነት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል። በ2011 ዓ.ም. ግማሽ ሚሊዮን ቶን የነበረው ዓመታዊ የቡና ምርት 2017 ዓም ላይ ወደ 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ቶን የሚጠጋ ምርት ማግኘት በመቻሉ ኢኮኖሚው ላይ ያለውን ከፍ ያለ አስተዋጽኦ ማስቀጠል ችሏል። በመሆኑም፣ የተያዘውን የተቀናጀ የልማት ስትራቴጂ በተግባር በመተርጎም የቡናን ምርት በጥራትና በብዛት ማሳደግ፣ የሀገሪቱን የማክሮ-ኢኮኖሚ መረጋጋት ከመደገፍ ባለፈ የኢትዮጵያን ቡና የወደፊት ጉዞ እና ዓለም አቀፋዊ መሪነት እጅግ አስተማማኝ ያደርገዋል።
በክልሉ ከእንስሳት ሀብት የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ ለእንስሳት ጤና ትኩረት ተሰጥቷል
Aug 13, 2026 129
ጂንካ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከእንስሳት ሀብት የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ ለእንስሳት ጤና ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡ በክልሉ ዲመካ ከተማ ከ446 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ለሚገነባው የዲመካ ክልላዊ የእንስሳት ጤና ላቦራቶሪ ዛሬ የመሰረት ድንጋይ ተቀምጧል። የመሰረት ድንጋዩን ያስቀመጡት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ በክልሉ ከእንስሳት ሀብት የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ ለእንስሳት ጤና ትኩረት ተሰጥቷል፡፡ በክልሉ የእንስሳት እርባታ በተለይ የአርብቶ አደሩ የኑሮ መሰረት በመሆኑ የእንስሳትን ጤና መጠበቅ የአርብቶ አደሩን ሕልውና መጠበቅ መሆኑን ተናግረዋል። ዲመካ ላይ የሚገነባው የእንስሳት ጤና ላቦራቶሪ ከአካባቢው አልፎ ለክልሉም ጥቅም የሚሰጥና ለእንስሳት ጤና መጠበቅ ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አመልክተዋል። የላቦራቶሪ ፕሮጀክቱ ግንባታ በተያዘለት የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ይደረጋል ብለዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ የአርብቶ አደር አደጋ ሥጋት ቅነሳና አካታች የኢኮኖሚ እሴት ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ ዶክተር ስዩም መታፈሪያ በበኩላቸው እንዳሉት፤ የዲመካ ክልላዊ የእንስሳት ጤና ላቦራቶሪ ድንበር ዘለል የእንስሳት በሽታዎችን ለመከላከልና አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል ነው። ለግንባታው ከ446 ሚሊዮን ብር በላይ መመደቡን ጠቅሰው፣ ላቦራቶሪው በመንግሥት እና በዓለም ባንክ ድጋፍ እንደሚገነባ አስታውቀዋል። ግንባታውን በአንድ ዓመት ከ6 ወር ጊዜ ለማጠናቀቅ መታቀዱን ገልጸው፣ ላቦራቶሪው የእንስሳት በሽታ ምልክቶች ሲኖሩ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት ያስችላል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪ ከዚህ ቀደም በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ወዳሉ ሀገር አቀፍ የእንስሳት ጤና ላቦራቶሪዎች ናሙና በመላክ ሲባክን የነበረውን ጊዜና ገንዘብ ለመቆጠብ ያስችላል ብለዋል።
የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ርብርብ እየተደረገ ነው
Aug 13, 2026 127
ባህርዳር፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ርብርብ ሲደረግ መቆየቱን የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ፡፡ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ለ19 ሺህ 698 የከተማዋ ነዋሪዎች የመኖሪያ ቤት ተጠቃሚ የሚያደርግ ቦታ ለመስጠት የእጣ ማውጣት ስነ ስርአት አካሂዷል። የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው በስነ ስርአቱ ላይ ባስተላለፉት መልእክት ዜጎችን የመኖሪያ የቤት ባለቤት የማድረግ ጉዳይ ከመንግስት የሰው ተኮር ፕሮጀክት አንዱ ነው። የባህር ዳር ከተማን እድገት ለማፋጠን ከሚከናወነው የመሠረተ-ልማት ግንባታ ጎን ለጎን የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ርብርብ ሲደረግ መቆየቱን ተናግረዋል። በዛሬው ዕለትም በመንግሥት የትኩረት አቅጣጫ መሠረት በ901 ማህበራት ለተደራጁ 19 ሺህ 698 ዜጎች የብሎክ ዕጣ ማውጣት መቻሉን አስታውቀዋል። የብሎክ ዕጣ ማውጣት የተቻለው የከተማ አስተዳደሩ ለቤት መስሪያ የሚሆን ቦታ አስፈላጊውን ካሳ በመክፈልና ከሦስተኛ ወገን ነፃ በማድረጉ መሆኑንም አመልክተዋል። ከዚህ ቀደም እስከ 10 ዓመት ድረስ ይቆይ የነበረውን የቤት መስሪያ ቦታ የማቅረብ ሂደት አሁን ላይ በቴክኖሎጂ በመታገዝ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ማቅረብ የሚያስችል አቅም መፈጠሩን ገልጸዋል። ይህም ዜጎች ተረጋግተው ተግባራቸውን እንዲከውኑ ለማድረግ ከማስቻሉም በላይ ከተማዋን ለኑሮ፣ ለንግድና ለኢንቨስትመንት የተመቸች ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። የቤት መስሪያ ቦታው የሚሰጠው በወረብ፣ በአዲስ ዓለም፣ በመኮድና በሰልቸል ሳይቶች መሆኑንም አብራርተዋል። የቦታው ተጠቃሚ የሚሆኑ ዜጎች ፈጥነው ወደ ግንባታ በመግባት ለወጣቶች የሥራ ዕድል፣ ለራሳቸውም ሀብት እንዲፈጥሩ አቶ ጎሹ አሳስበዋል። በዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የከተማ አስተዳደሩ፣ የክልሉ ባለድርሻ አካላት እና የማህበራት ተጠቃሚ አባላት ተገኝተዋል።
በብሄረሰብ አስተዳደሩ ዘግይቶ የጣለውን ዝናብ በማቀብ ለሰብል ልማት ለማዋል ርብርብ እየተደረገ ነው
Aug 13, 2026 119
ሰቆጣ ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዘግይቶ የጣለውን ዝናብ በማቀብ ለሰብል ልማት ለማዋል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የአስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ገለፀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አብዛኛው በአስተዳደሩ ስር ያሉ አካባቢዎች ዝናብ አጠር በመሆናቸው የዝናብ እጥረቱን በመቋቋም ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሠራ ይገኛል። በዚህም 120 ሺህ 638 ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን በተደረገ ጥረት እስካሁን 80 በመቶ ያህሉን ማሳካት መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ከተዘራው መሬት ውስጥም 57 ሺህ 612 ሄክታሩ ድርቅን የሚቋቋሙና ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን በመለየት ማልማት መቻሉንም አመልክተዋል። አርሶ አደሩ እስከ አሁን ባከናወናቸው ተግባራትም ከ9 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ የእርጥበት እቀባ ሥራ ማከናወኑን ተናግረዋል። ከአካባቢው የአየር ጸባይ መለዋወጥና የዝናብ መቆራረጥ ጋር ተያይዞ ሊከሰት የሚችል ተባይን ለመከላከል ግብረ-ኃይል ተቋቁሞ ወደ ሥራ መግባቱን ጠቁመዋል። አርሶ አደሩ የእርጥበት እቀባውን አጠናክሮ እንዲቀጥልና ሰብሉን ከተባይና ከአረም እንዲከላከል የግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራ እየተሠራ እንደሚገኝም አስረድተዋል። የጋዝጊብላ ወረዳ 06 ቀበሌ ነዋሪዎቹ አርሶ አደር እምወደው አየለ እና አርሶ አደር ደስታነህ ንጉሡ በበኩላቸው፤ የዝናብ እጥረቱን ለመቋቋም በእርሻቸው ላይ ውሃ የሚያቁሩ ጉድጓዶችን መቆፈራቸውን ተናግረዋል። ከባለሙያ የሚሰጣቸውን ምክረ-ሐሳብ መሠረት በማድረግ ሰብላቸውን በወቅቱ ዘርተው አሁን ላይ ወደ አረም ሥራ መግባታቸውንም ገልጸዋል። በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በ2018/2019 የመኽር እርሻ ወቅት 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በሰሜን ሸዋ ዞን በማዕድን ሀብት ልማት አበረታች ውጤት እየተመዘገበ ነው
Aug 13, 2026 103
ደብረ ብርሃን፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በሰሜን ሸዋ ዞን የማዕድን ሀብትን አልምቶ ጥቅም ላይ በማዋል አበረታች ውጤት እየተመዘገበ መምጣቱን የዞኑ የማዕድን ሀብት ልማት መምሪያ ገለጸ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ታደሰ በቀለ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንዳሉት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የባህላዊ ማዕድናት ምርትና ግብይት ሕጋዊ መስመር ተከትሎ እንዲከናወን ተደርጓል። በዚህም 7 ነጥብ 7 ሚሊዮን ቶን ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ እንደተቻለ ነው ያመለከቱት። የኢንዱስትሪ፣ የኮንስትራክሽንና የከበሩ ማዕድናት በጥራት ተመርተው ለገበያ ማቅረብ በመቻሉም ከ4 ነጥብ 4 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማዳን እንደተቻለ ገልጸዋል። ከዚህም ባለፈ በአካባቢው ጂፕሰም፣ ላይምስቶንና ኦፓልን ጨምሮ ከ27 በላይ የከበሩና የኢንዱስትሪ ማዕድናት መኖራቸውን ጥናት ማረጋገጥ መቻሉን ተናግረዋል። በቀጣይም ዘርፉን በዘመናዊ መንገድ ለመምራትና የግብይት እሴትን ለማጠናከር በጣርማበር ወረዳ የከበሩ ማዕድናት መግዣና መሸጫ የገበያ ማዕከል እየተገነባ ይገኛል ብለዋል። የአካባቢውን ማህበረሰብ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለማድረግና የስራ ዕድል ለመፍጠር በግል እና በኢንተርፕራይዝ ለተደራጁ 247 ባህላዊ ማዕድን አምራች ማህበራት የስራ ፈቃድ መሰጠቱንም አክለው ገልጸዋል። በእንሳሮ ወረዳ የ"ሽመልስ ማሞ እና ጓደኞቻቸው" ህብረት ሽርክና ማህበር ሰብሳቢ አቶ ሽመልስ ማሞ በበኩላቸው፤ ማህበሩ ለግንባታ አገልግሎት የሚውል ማዕድን አምርቶ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆኑን ተናግረዋል። ማህበሩ 47 አባላት ያሉት ሲሆን፣ የማዕድን ሀብቱን አምርቶ ከሚገኘው ሽያጭ አባላቱን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። በመርሐቤቴ ወረዳ ቁም አምባ ቀበሌ “ሲልካ“ የተባለ ለጠርሙስ ምርት በግብዓትነት የሚያገለግል ማዕድን እሴት ጨምረው በማቅረብ ተጠቃሚ እንደሆኑ የገለጹት ደግሞ የ"ማክን ትሬዲንግ" ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ ሙሉጌታ ደምሴ ናቸው። ድርጅታቸው አሁን ላይ ከ100 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፍጠሩን ጠቅሰው፤ በቀጣይም ምርታቸውን በተሻለ ፍጥነትና ጥራት ለገበያ ለማቅረብ እየሰሩ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በክልሉ ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ወደ ሥራ ገብተዋል
Aug 13, 2026 211
ሚዛን አማን፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በ2018 በጀት ዓመት ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ፈቃድ ወስደው ወደ ሥራ መግባታቸውን የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ምክትልና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ከበደ ተስፋዬ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ክልሉ ለኢንቨስትመንት ሥራ ያለውን አቅም በሚገባ ለመጠቀም በተሰጠው ትኩረት ውጤት እየተገኘ ነው። በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች በግብርና፣ በአገልግሎት እና በኢንዱስትሪ ዘርፍ ለመሰማራት ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት ፈቃድ መሰጠቱን ተናግረዋል። ፈቃድ ከተሰጣቸው 123 ባለሀብቶች መካከል 63ቱ በግብርና ዘርፍ መዋለንዋያቸውን ለማፍሰስ ፈቃድ የወሰዱ ሲሆን ይህም የክልሉን ጸጋ መሠረት ያደረገ መሆኑን አመልክተዋል። በአገልግሎት ዘርፍ በከተሞች የተሻለ ለውጥ እየተመዘገበ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ከበደ፣ በኢንዱስትሪ ዘርፍ ያለውን ውስንነት ለመሙላት የሚያስችል የተቀናጀ እንቅስቃሴ መጀመሩን ጠቁመዋል። በበጀት ዓመቱ ወደሥራ ለገቡ ባለሀብቶች ከ16 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት እንደተላለፈና ከ110 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩንም ተናግረዋል። ለባለሀብቶቹ የሥራ ፈቃድ ከመስጠት ባሻገር ለልማት ፕሮጀክቶቻቸው ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ የተናገሩት ኃላፊው በትላልቅ የኢንዱስትሪ ዘርፎች ለሚሠማሩ ባለሀብቶች ክልሉ ልዩ ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። በክልሉ ሚዛን አማን ከተማ በሆቴልና ቱሪዝም ኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ዋለልኝ ቸርነት በበኩላቸው፤ መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ወደ ተግባር መግባታቸውን ገልጸዋል። አካባቢው ከፍተኛ የንግድ እና ሌሎች ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ያለበት መሆኑ ለኢንቨስትመንት ሥራ ውጤታማነት የራሱን አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በከተማ አስተዳደሩ በኩል የተደረገላቸው የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ሥራቸውን በተሻለ ሁኔታ ለማከናወን አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ጠቁመዋል። መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የሰጠው ትኩረት በየመስኩ ኢኮኖሚው እንዲነቃቃ አድርጓል ያሉት ደግሞ በግንባታ ሥራ የተሰማሩት አቶ አንድነት ሀብተማርያም ናቸው። በተለይ በከተሞች በአገልግሎት መስጫ ኢንቨስትመንቶች ላይ እየመጣ ያለውን ለውጥ ተከትሎ የመብራት፣ የመንገድ፣ የውሃና ሌሎች መሠረተ ልማቶች አብረው እየተስፋፉ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ለተሰማሩበት የግንባታ ዘርፍ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር ባሻገር ለከተሞች መስፋፋትና ለአካባቢው ዕድገት በጎ አሻራ ያሳርፋል ብለዋል፡፡
በሐረሪ ክልል የኢንቨስትመንት ፍቃድ እና መሬት ወስደው ወደ ግንባታና ማምረት ባልገቡ 12 ባለሀብቶች ላይ እርምጃ ተወሰደ
Aug 13, 2026 81
ሐረሪ ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል የኢንቨስትመንት ፍቃድ እና መሬት ወስደው ወደ ግንባታና ማምረት ባልገቡ 12 ባለሀብቶች ላይ የኢንቨስትመንት ፍቃድ ስረዛና እገዳ እርምጃ መወሰዱን የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሀምዲ ሰለሃዲን ለኢዜአ እንዳሉት የክልሉ መንግሥት በኢንቨስትመንት ተሰማርተው ለሚገኙና አዳዲስ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች ምቹ ሁኔታን እየፈጠረ ይገኛል። ከዚህም ባለፈ የባለሀብቶች እንቅስቃሴ ያለበትን ሁኔታ የመስክ ምልከታ በማከናወን በገቡት ውል መሰረት ወደ ስራ ያልገቡ ባለሃብቶች ላይ እርምጃ እየወሰደ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ባለሀብቱ ከመንግስት የኢንቨስትመንት ፈቃድና መሬት የሚወስደው የክልሉን ልማት ለማፋጠን በመሆኑ የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባም ነው ያሳሰቡት። በዚህም በክልሉ በኢንቨስትመንት አዋጅ፣ ደንብና መመሪያ መሠረት ቀደም ሲል የኢንቨስትመንት ፈቃድና መሬት ወስደው ወደስራ ያልገቡና ግንባታ ያጓተቱ 3 ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰረዙን ተናግረዋል። እንዲሁም መሬት ወስደው በውሉ መሠረት ወደ ግንባታ ሥራ ባልገቡና የሼድ ግንባታ አጠናቀው ወደ ማምረት ባልገቡ 9 ባለሀብቶች ላይ ደግሞ ፈቃድ የማገድ እርምጃ መውሰዱን አስታውቀዋል። ከዚህ በተጨማሪም የኢንቨስትመንት ፈቃድና መሬት ወስደው አዝጋሚ የግንባታ ሂደት ውስጥ ለሚገኙ 7 ባለሀብቶችም የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷል ብለዋል። በባለሀብቶቹ ላይ ከሚወሰደው እርምጃ ጎን ለጎንም ባለሀብቶቹ የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች የመፍታት ሥራ ተከናውኗል ሲሉ ተናግረዋል። በባለሀብቶቹ ላይ እርምጃ መወሰድ መጀመሩም የሌሎች ፕሮጀክቶች ግንባታ ሥራዎች እንዲፋጠኑ ዕድል መፍጠሩን ጠቁመው በቀጣይም መሰል እርምጃዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አመልክተዋል። በቀጣይም ባለሀብቶቹ ወደ ሥራ ካልገቡ ፈቃድ በመሰረዝ የወሰዱት መሬት ለመሬት ባንክ ገቢ እንደሚደረግ አስታውቀዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ ከ3 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ላስመዘገቡ 96 ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠቱን ጠቅሰዋል። ለባለሀብቶቹም የኢንቨስትመንት ፈቃድ የተሰጣቸው በማኑፋክቸሪንግ፣ ሆቴል፣ ግብርና፣ በገበያ ማዕከልና በሌሎች ዘርፎች ለመሰማራት ጥያቄ በማቅረባቸው መሆኑን ተናግረዋል።
በጉራጌ ዞን የሌማት ትሩፋት መርሃግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን እያሳደገ ነው
Aug 13, 2026 78
ወልቂጤ፣ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ) ፡-በጉራጌ ዞን የሌማት ትሩፋት መርሃግብር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን እያረጋገጠ መምጣቱን በዘርፉ የተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ በርካታ ዜጎች በዶሮ፣ በወተት፣ በከብት እርባታ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተው ምርታማነታቸውን እያሳደጉ ነው። መርሃ-ግብሩ በቤተሰብ ደረጃ የምግብና ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ምርትንና ምርታማነት በማሳደግ ገበያን ለማረጋጋትና ለዜጎች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ለመፍጠር እያስቻለ ነው። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጉራጌ ዞን በሌማት ትሩፋት መርሀግብር ተሰማርተው ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል በዶሮ እርባታ ዘርፍ የተሰማራችው ነፃነት በለጠ፣በአሁኑ ወቅት በእንቁላልና በሥጋ ዶሮዎች እርባታ መሰማራቷን ገልጻ፣ በቀን በአማካይ 200 እንቁላል ለገበያ በማቅረብ በምታገኘው ገቢ የተሻለ ተጠቃሚ መሆኗን ተናግራለች። ሌላኛው በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት የተሰማሩት አቶ ገብሩ ታፈሰ ጾሙን ሲያድር በነበረ 2 ሄክታር መሬት ላይ ልማታቸውን አጠናክረው በመቀጠል የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ ምርታቸውን ለገበያ ማቅረብ መጀመራቸውን ገልጸዋል። የረሻድና ቤተሰቦቹ የተቀናጀ እንስሳት ልማት ሥራ አስኪያጅ አብደራዛቅ ከድር እንደገለጹት፤ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በፈጠረላቸው ምቹ ዕድል በወተት ልማት፣ በእንስሳት እርባታና በንብ ማነብ ሥራ ተሰማርተው ውጤታማ ሆነዋል። የተቀናጀ የእንስሳት ልማት ምርታማ እንዳደረጋቸው ጠቅሰው፣ በወተት ልማቱ በቀን በአማካይ 60 ሊትር ወተት እንደሚያገኙ ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ ያረቧቸውን የሥጋ ከብቶች በመሸጥ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን ተናግረዋል። የጉራጌ ዞን አስተዳደር ግብርና መምሪያ በበኩሉ በዞኑ የሌማት ትሩፋት መርሀግብሩን ወጤታማ ለማድረግ ትኩረት ተሰጥቶ በተከናወኑ ሥራዎች አመርቂ ወጤት መመዝገቡን ተናግረዋል። የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ እና የግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ እንደገለጹት፤ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዞኑ በስፋት እየተተገበረ ይገኛል። በተለይም በወተትና በእንቁላል ምርትና መርታማነትን በማሳደጉ በአካባቢው የነበረውን የአቅርቦት እጥረት በመፍታት በኩል ጉልህ አስተዋጾ ከማድረግ ባለፈ በዘርፉ የተሰማሩትን የተሻለ ተጠቃሚ አድርጓቸዋል ብለዋል። መርሀግብሩን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ በአሁኑ ወቅት ዝርያቸው ለተሻሻሉ የወተት ላሞች አቅርቦትና ለዶሮ እርባታ ልማት ልዩ ትኩረት መሰጠቱንም አስታውቀዋል። ከዚህ በተጨማሪ በሌማት ትሩፋት ለተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ ከማገዝ ባለፈ በዘርፉ የሚሰማሩትን የህብረተሰብ ክፍሎች ቁጥር በማሳደግ ለማስፋፋት ይሰራል ብለዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በከተሞቹ የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል
Aug 13, 2026 79
ሆሳዕና ፤ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ) ፦ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ሆሳዕና፣ በቡታጅራና በወልቂጤ ከተሞች የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች መከናወናቸው ተመላከተ፡፡ የከተሞቹ አስተዳደሮች ከንቲባዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ያረጋገጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል። የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሳሙኤል ሽጉጤ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት አገልግሎትን ለማዘመን የሚያስችል መሶብ የአንድ ማዕከል፣ የጤና ተቋማት፣ የውስጥ ለውስጥ አስፋልት መንገድ እና የ12 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል ብለዋል፡፡ ይህም ከተማዋን ጽዱ፣ ውብና ለነዋሪው ምቹ፣ ለኢንቨስትመንትና ለኮንፈረንስ ቱሪዝም ተመራጭ እንድትሆን አስችሏል ነው ያሉት። የከተማው ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ መሰብሰብና የማህበረሰቡን ተሳትፎ ማዕከል ያደረጉ ስራዎችን ተግባራዊ የማድረጉ ሂደት በተያዘው በጀት ዓመትም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። የቡታጅራ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አብዱ አህመድ በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ የልማት ስራዎች ተግባራዊ መደረጋቸውን ተናግረዋል። አስተዳደሩ የማህበረሰቡን ተሳትፎና የውስጥ አቅምን በመጠቀም ተግባራዊ በማድረግ ላይ ከሚገኘው የ25 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ውስጥ 11 ነጥብ 26 ኪሎ ሜትሩ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል ነው ያሉት። ይህም ከተማዋን ለኑሮ ምቹ፣ ሳቢና ማራኪ ከማድረግ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዋ እንዲነቃቃ ማድረጉን ገልጸዋል። በከተማው እየተተገበረ የሚገኘው የኮሪደር ልማት ስራ ወልቂጤን ለነዋሪዎቿ ምቹና ተመራጭ እንድትሆን አድርጓታል ያሉት ደግሞ የከተማዋ ከንቲባ ሙራድ ከድር ናቸው። በልማት ስራውም የማህበረሰቡ ተሳትፎና ተጠቃሚነት እያደገ መምጣቱን እንዲሁም የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ በ2019 ዓ/ም የትኩረት አቅጣጫ ዙሪያ ከክልል፣ ከዞንና ከከተማ አስተዳደር አመራሮች ጋር በቡታጅራ ከተማ የምክክር መድረክ ማካሄዱ ይታወሳል።
ማዕከሉ ከእንስሳት ሀብት የሚገኘውን የኢኮኖሚ ጥቅም ለማሳደግ ሚናው የጎላ ነው
Aug 13, 2026 88
ጂንካ፣ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኦሞ ዞን በና ፀማይ ወረዳ የቀይ-አፈር የኤክስፖርት እንስሳት ማሰባሰቢያ ማዕከል መገንባት አርብቶ አደሩና ሀገር ከእንስሳት ሀብት ተገቢውን የኢኮኖሚ ጥቅም እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑ ተገለጸ። በበና ፀማይ ወረዳው የተገነባው የቀይ-አፈር የኤክስፖርት እንስሳት ማሰባሰቢያ ማዕከል ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ የአርብቶ አደር አደጋ ሥጋት ቅነሳና አካታች የኢኮኖሚ እሴት ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ ስዩም መታፈሪያ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ ተገንብቶ ለምረቃ የበቃው የቀይ-አፈር የኤክስፖርት እንስሳት ማሰባሰቢያ ማዕከል ከ70 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተደርጎበታል። ማዕከሉ በሀገሪቱ ለሚገኙ 13 የኤክስፖርት ቄራዎች የእርድ እንስሳትን ለማቅረብ ታስቦ የተገነባ መሆኑንም ተናግረዋል። ማዕከሉ የእንስሳት ክሊኒክ፣ መኖ ማከማቻ መጋዘኖችን ጨምሮ እንስሳቱን በክብደት፣ በተክለሰውነትና በዝርያ መለየት የሚያስችሉ ክፍሎችን አካቶ የተገነባ መሆኑንም አንስተዋል። የማዕከሉ መገንባት እንስሳቱን ያለ ደላላ በቀጥታ ለገበያ በማቅረብ አርብቶ አደሩ ለእንስሳቱ ተገቢውን ዋጋ እንዲያገኝ ያደርጋል ብለዋል። በተጨማሪም ሀገሪቱ የእንስሳት ኤክስፖርትን በማሻሻል ከእንስሳት ሀብቷ ተገቢውን ጥቅም እንድታገኝ የሚያስችል መሆኑን ነው የገለጹት። በማዕከሉ ያለው ክሊኒክም እንስሳቱ ከመሸጣቸው በፊት አስፈላጊው የሕክምና ክትትልና እንክብካቤ በማድረግ ጥራታቸውን ለማስጠበቅ ያግዛል ብለዋል። የበናፀማይ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዮሐንስ ጋርሾ በበኩላቸው ማዕከሉ ለአርብቶ አደሩ የተሻለ ተጠቃሚነት ትልቅ እድል ይዞ መምጣቱን ነው የገለጹት። የአካባቢው አርብቶ አደር በርካታ ከብቶች ቢኖሩትም በህገወጥ ንግድና በገበያ ትስስር ችግር ተገቢውን ጥቅም ሳያገኝ መቆየቱን አስታውሰው፣ የማዕከሉ መገንባት እነዚህን ችግሮች ይፈታል ብለዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሕብረት ሥራ ኤጀንሲ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ዮሐንስ ቱሬ በበኩላቸው ኤጀንሲው የኤክስፖርት ስታንዳርድን የጠበቁ የቁም እንስሳትን ከገበያ ማዕከላት በማሰባሰብ በሀገሪቱ ለሚገኙ የኤክስፖርት ቄራዎች እንደሚያቀርብ ተናግረዋል። የእንስሳት ማሰባሰቢያ ማዕከሉ ወደአገልግሎት መግባት እንስሳት በህገ-ወጥ መንገድ ድንበር ተሻግረው እንዳይሸጡ በማድረግ ህጋዊ የንግድ ሥርዓትን ያጠናክራል ተብሏል። በተጨማሪም ደረጃቸውን የጠበቁ የኤክስፖርት እንስሳትን ለውጭ ገበያ በማቅረብ የሀገርን የውጭ ምንዛሬ ገቢ ለማሳደግ ፋይዳው የጎላ ነው። በማዕከሉ የምረቃ መርሀግብር ላይ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩን (ዶ/ር) ጨምሮ የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ እና፣ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ሥራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል።
ስንዴን በኩታገጠም በማልማታችን ምርታማነታችንን እያሳደግን ነው
Aug 13, 2026 89
ሸገር፤ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፡- በሸገር ከተማ የኩራ ጂዳ ክፍለ ከተማ አርሶ አደሮች በዘመናዊ መንገድና በኩታገጠም የስንዴ ልማት ምርታማነታቸው መጨመሩን ገለጹ። በኢትዮጵያ በስንዴ ምርት ራስን ለመቻልና ሀገራዊ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በተቀየሰው ስትራቴጂ መሠረት፣ በኦሮሚያ ክልልና በሸገር ከተማ አስተዳደር የስንዴ ልማትን በስፋት የማስፋፋት ሥራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል። በተለይም በሸገር ከተማ ኩራ ጂዳ ክፍለ ከተማ የሚገኙ አርሶ አደሮች ቀደም ሲል ይጠቀሙበት የነበረውን ባህላዊና አነስተኛ ይዞታን መሠረት ያደረገ የአመራረት ዘዴ በመተው፣ አቅማቸውን አዋህደው በኩታገጠም በማልማት ላይ ይገኛሉ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ አርሶ አደሮቹ የስንዴ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ከግብርና ሙያተኞች ያገኙትን ግንዛቤና ድጋፍ በመጠቀም ስኬታማ ሥራ እየሠሩ ይገኛሉ። ከአርሶ አደሮቹ መካከል ወጣት ደቡ ሱልጣን እንደተናገረው፤ ባለፉት ዓመታት የግብርና ሥራችን ያልዘመነና ከፍተኛ ድካም የነበረበት ነው ይላል። በአሁኑ ወቅት ግን በቴክኖሎጂ የተደገፈ የኩታገጠም ግብርና መካሄዱ ከፍተኛ ውጤት እያስገኘልን ነው ብሏል። አርሶ አደር ቡርኩ ታደሰ በበኩላቸው፤ ለዚህ ዓመት የግብርና ሥራ የሚያስፈልጉ ግብአቶች በወቅቱ በመቅረባቸው፣ በበለጠ ተግተን በልማት ሥራችን ላይ ተሰማርተናል ብለዋል። አርሶ አደሩ በአካባቢያችን በኩታ ገጠም በመደራጀትና ያሉንን አቅሞች በማቀናጀት በልማቱ መሰማራታችን ቀድሞ ከምናገኘው ምርት የበለጠ በማግኘት ተጠቃሚ ሆነናል ብለዋል። ሌላኛው አርሶ አደር ወጣት ተስፋዬ በቀለ አክሎ እንደገለጸው፤ የኩታ ገጠም ልማት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ጠቁሞ፣ ይህም አርሶ አደሩ ሕይወቱን ከመቀየር ባሻገር ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ለከተማዋ ኢኮኖሚ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው ነው ብሏል። በልማቱ ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች አስፈላጊው ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑና የግብርና ግብአቶችንም በወቅቱ ማግኘታቸው ለሥራቸው ትልቅ መነሳሳት እንደሆናቸው ተናግረዋል። በሸገር ከተማ የስንዴ ልማትን ማጠናከር የአርሶ አደሮችን ሕይወት ከመቀየር ጎን ለጎን፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የከተማዋን ኢኮኖሚ እድገት ለማፋጠን ከፍተኛ ሚና ያለው መሆኑን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የከተማዋ የግብርና እና ልማት ክላስተር አስተባባሪ አቶ ግርማ ሀይሉ መግለጻቸው ይታወሳል። በከተማዋ ኩራ ጂዳ ክፍለ ከተማ በ340 ሄክታር መሬት ላይ በኩታገጠም አሰራር ለምርጥ የስንዴ ዘር ብዜት የሚሆን የዘር መዝራት ስራ ትናንት ተከናውኗል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከመስህብ ስፍራ ጎብኝዎች ሁለት ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ ተገኘ
Aug 13, 2026 68
ሳጃ፤ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ባለፈው በጀት ዓመት ከ967 ሺህ በላይ የመስህብ ስፍራ ጎብኚዎች ሁለት ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ መገኘቱን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ። “የባህልና ቱሪዝም እመርታ ለክልላችን ሁለንተናዊ ከፍታ” በሚል መሪ ሐሳብ የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት እቅድ አፈፃፀም እና የ2019 በጀት ዓመት ጠቋሚ እቅድ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በሳጃ ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩም የቢሮው ኃላፊ አቶ ሳሙኤል መንገሻ እንደገለፁት፤ በ2018 በጀት ዓመት በክልሉ የሚገኙ ተፈጥሯዊ፣ ታሪካዊና ባህላዊ መስህብ ስፍራዎችን የማልማት፣ የማስተዋወቅና ለጎብኚዎች ምቹ የማድረግ ስራዎች በስፋት ተከናውነዋል፡፡ ይህም በበጀት ዓመቱ የቱሪስት ፍሰቱ እንዲጨምር ምክንያት ከመሆን ባሻገር ለክልሉ ኢኮኖሚ ተጨማሪ አቅም መፍጠር ማስቻሉን ጠቁመው ከ967 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች የመስህብ ስፍራዎችን መጎብኘታቸውን ተናግረዋል። ከጎብኚዎቹ ውስጥ 17 ሺህ 500 የውጪ ጎብኚዎች መሆናቸውን ገልጸው ከዚህም ከ1 ቢሊዮን 850 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልፀዋል። ባለፈው በጀት ዓመት በክልሉ የሚገኙ የመስህብ ስፍራዎችን የማልማት ተግባር በተጠናከረ ሁኔታ መከናወኑን ተናግረው የጢያ አለም አቀፍ ቅርስን ጨምሮ 5 የቱሪዝም መዳረሻ ስፍራዎች በ6 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ወጪ ለጎብኚዎች ምቹ የማድረግ ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በክልሉ ከ295 በላይ መዳረሻ ስፍራዎች መኖራቸውን ጠቁመው 1 ሺህ 805 የመስህብ ዓይነቶችን በመለየትና በማደራጀት የመስህብ ስፍራ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝም አስረድተዋል። በብልጽግና ፓርቲ የየም ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አብርሃም ዝናብ በበኩላቸው በዞኑ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በመለየት፣ በማልማት እና በማስተዋወቅ የዞኑን መልካም ገፅታ ከመገንባት ባሻገር ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ የማሳደግ ተግባር እየተከናወነ ነው ብለዋል። በዞኑ በየዓመቱ ጥቅምት 17 የሚከናወነው ባህላዊ የመድኃኒት ለቀማ ''ሳሞኤታ'' የህዝቡን ሃገር በቀል እውቀት አጉልቶ በማሳየት ለዞኑ የቱሪዝም ዕድገት ትልቅ ድርሻ እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል። በውይይት መድረኩም የክልሉ፣ የዞንና የልዩ ወረዳ አመራሮች እና የሚመለከታቸው አካላት እየተሳተፉ ነው።
በኦሮሚያ ክልል ባለፉት አምስት ዓመታት ከ96 ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች ተገንብተው ለአገልግሎት በቅተዋል -አቶ አወሉ አብዲ
Aug 13, 2026 76
ጅማ፤ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል የሕዝቡን እርካታ የሚያረጋግጡና የአገልግሎት አሰጣጡን የሚያዘምኑ ዘመናዊ ተቋማትን የመገንባትና የማደራጀት ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አወሉ አብዲ ተናገሩ። በኢትዮጵያ በየደረጃው የሚገኙ የመንግሥት ተቋማት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚታዩ የመልካም አስተዳደር፣ የቢሮክራሲና የዘመናዊ አሰራር እጥረት ችግሮችን በዘላቂነት ለመቅረፍ ሀገራዊ የሪፎርም ሥራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል። በዚህም መሠረት በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ጥቂት ዓመታት የሕዝቡን እርካታ የሚያረጋግጡ፣ አሰራርን ግልጽና ቀልጣፋ የሚያደርጉ እንዲሁም የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን መሠረት ያደረጉ ተቋማዊ ማሻሻያዎች ተደርገዋል። ይህ የአገልግሎት አሰጣጥን የማዘመንና ዘመናዊ ተቋማትን የመገንባት እንቅስቃሴም የቢሮክራሲ እንግልትንና ሙስናን በመቀነስ፤ አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝ በማድረግ፣ ዘመናዊ የአገልግሎት ማዕከላትን በመገንባትና የመንግሥት መዋቅርንና የሰው ኃይል አቅምን በማሳደግ ረገድ ውጤቶች እንዲመዘገቡ አስችለዋል። በአጠቃላይ በክልሉ የሚከናወኑት እነዚህ የቴክኖሎጂና የተቋማት ግንባታ ሥራዎች የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ከመመለሳቸው ባሻገር፣ ለክልሉ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች መፋጠን ምቹ ሁኔታን እየፈጠሩ ይገኛሉ። በዛሬው ዕለትም የዚሁ ጥረት አካል የሆነው እና ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገበት የጅማ ዞን አስተዳደር ጽህፈት ቤት ህንፃ ተመርቋል። በምረቃው ላይ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዝደንት አወሉ አብዲ፣ በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሃላፊ ነመራ ቡሊ እና የተለያዩ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል። አቶ አወሉ አብዲ፤ ባለፉት አምስት ዓመታት በተሰሩ ስራዎች ከ96ሺህ በላይ የልማት ፕሮጀክቶች ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ ነው ብለዋል። ፕሮጀክቶቹም የህብረተሰቡን ጥያቄ ባማከለ መልኩ የተገነቡ መሆናቸውንም አክለዋል። ከዚህ በተጨማሪም በክልሉ 96 መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎቶች ተገንብተው የተቀላጠፈ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ ነው ያሉት። "ወደፊትም ለህዝባችን የገባነውን ቃል በተግባር የመወጣት ሀላፊነታችንን ለማሳካት በትጋት እንሰራለን" ብለዋል። በአጠቃላይ በክልሉ በመደመር እሳቤ የተተገበሩ ተግባራት በፖለቲካ፣ በማህበራዊና በኢኮኖሚው ዘርፎች ትልቅ ለውጥ አምጥተዋል ብለዋል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሀላፊ ነመራ ቡሊ በበኩላቸው፤ ብልፅግና ፓርቲ በክልሉ ጠንካራ ኢኮኖሚን ለመገንባት እና ትምህርትና ቴክኖሎጂን ለማስፋፋት እንዲሁም ዘመናዊ አገልግሎት ለመስጠት ያደረጋቸው ጥረቶች ውጤታማ ናቸው ብለዋል። ባለፉት ስድስት እና ሰባት ዓመታት በክልሉ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ እድገት መመዝገቡንም ለአብነት አንስተዋል። ከዚህ በተጨማሪም ምርታማነትን በማሳደግ እና የስራ ዕድልን በማስፋት ረገድ ፓርቲው ለህዝብ የገባውን ቃል እየተወጣ መሆኑን አክለዋል። ዛሬ የተመረቀው የአስተዳደር ህንፃ 125 ክፍሎች ያሉት እና 17 የመንግስት ሴክተሮች አገልግሎት የሚሰጡበት መሆኑን የገለጹት ደግሞ የጅማ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ቲጃኒ ናስር ናቸው።
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በመኸር እርሻ ከ500 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Aug 13, 2026 82
ጎንደር፤ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በመኸር እርሻ ከ500 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና በመምሪያ ገለጸ። በዞኑ በ2018/2019 የምርት ዘመን ከ586 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር በመሸፈን ምርታማነትን ለማሳደግ ግብ የመምሪያው ኃላፊ አቶ ንጉሤ ማለደ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴ የተሻሻሉ አሠራሮችና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም 501 ሺህ ሄክታር መሬት በዘር መሸፈን ተችሏል። በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥ በቆሎ፣ ገብስ፣ ስንዴ፣ ጤፍና ሰሊጥ እንዲሁም ሌሎች የሰብል ዘሮች እንደሚገኙበት ተናግረዋል። በምርት ዘመኑ የመካናይዜሽን እርሻን በማስፋፋት በትራክተር ለማረስ ከታቀደው ከ71 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ውስጥ እስካሁን 94 በመቶውን ማሳካት መቻሉንም ገልጸዋል። በአጠቃላይ በምርት ዘመኑ ለማልማት ከታቀደው መሬት ከ24 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይሰበሰባል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል። በአሁኑ ወቅት ለምርት ዘመኑ ከቀረበው ከ627 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ 403 ሺህ ኩንታሉ ለአርሶ አደሮች ተሰራጭቶ ጥቅም ላይ መዋሉን አመልክተዋል። ዝናብ ዘግይቶ መጣል በጀመረባቸው አካባቢዎች የተገኝውን እርጥበትን በመጠቀም በአጭር ጊዜ የሚደርሱ ሰብሎችን አርሶ አደሩ ለይቶ እንዲያለማ ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገ እንደሚገኝም አብራርተዋል። በዞኑ ጠገዴ ወረዳ በእርሻ ኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ሽባባው መሪድ በበኩላቸው፤ የመካናይዜሽን እርሻን በመጠቀም ከ500 ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈናቸውን ተናግረዋል። መሬቱን ያለሙት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ባላቸው አኩሪ አተር፣ ጥጥ፣ ሰሊጥና ማሽላ መሆኑን ጠቅሰው፤ እስከ 8 ሺህ ለሚደርሱ ዜጎችም ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል። የሰው ጉልበትን በዘመናዊ የእርሻ ትራክተር በመተካት የሰብል ምርታማነታቸውን ማሳደጋቸውን የገለጹት ደግሞ በዚሁ ወረዳ በእርሻ ኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ቸሬ ገብሬ ናቸው። የተረከቡትን 77 ሄክታር መሬት ቀድመው በማለስለስ በጥጥና በአኩሪ አተር ሰብሎች ሸፍነው እያለሙ መሆናቸውን አስረድተዋል። በዞኑ በ2017/2018 የምርት ዘመን ከለማው 552 ሺህ 895 ሄክታር መሬት 18 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል ምርት መገኘቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው ላሞች በይርጋዓለም ከተማ የወተት አልሚዎችን ተጠቃሚነት አሳድገዋል
Aug 13, 2026 79
ይርጋለም፤ ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፡-የተሻሻለ ዝርያ ካላቸው ላሞች በሚያገኙት የወተት ምርት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው ማደጉን በወተት ልማት ዘርፍ የተሰማሩ የይርጋዓለም ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ በበኩሉ በክልሉ በእንስሳት ሀብት ልማት ዘርፍ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ የተለያዩ ተግባራት በመከናወናቸው አመርቂ ውጤት መመዝገቡን ገልጿል፡፡ በማዕከላዊ ሲዳማ ዞን ይርጋዓለም ከተማ በወተት ልማት ዘርፍ የተሰማሩ ነዋሪዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የተሻሻለ ዝርያ ካላቸው ላሞች የሚያገኙት የወተት ምርት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን አሳድጎታል። ከተጠቃሚዎቹ መካከል አቶ ደሳለኝ ጥላሁን የወተት ልማት ሥራቸውን የተሻሻለ ዝርያ ባላቸው አነስተኛ የወተት ላሞች እንደጀመሩ ገልጸዋል። በሂደት ሥራቸውን በማስፋፋት በአሁኑ ወቅት የላሞችና ጊደሮቻቸውን ቁጥር ከ30 በላይ ለማድረስ እንደቻሉ ገልጸው፣ በዘርፉ ተገቢ ትኩረት ተሰጥቶ ከተሰራ ትርፋማ መሆን ይቻላል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በቀን ከ500 ሊትር በላይ የወተት ምርት እንደሚያገኙ ገልፀው፣ ከሌሎች ጋር በማህበር ተደራጅተው የወተት ምርቶቻቸውን ለኢንዱስትሪዎችና ለአካባቢው ማህበረሰብ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። መንግስት የከብቶቻቸውን ጤና ከመጠበቅ ጀምሮ ውጤታማ እንዲሆኑ አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል እያደረገላቸው መሆኑንም አመልክተዋል። ሌላኛው ነዋሪ አቶ ደረጀ ኤጃሞ ሥራውን የተሻሻለ ዝርያ ባለት አንድ የወተት ላም እንደሆነ ተናግረው ከመንግስት የተመቻቸላቸውን የብድርና የቦታ ድጋፍ ተጠቅመው ጠንክረው በመስራታቸው ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የላምና የጊደሮችን ቁጥር 36 ማድረሳቸውን ጠቅሰው፣ እንስሳቶቻቸውን በበቂ ሁኔታ ለመመገብ ከሁለት ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የተለያዩ የእንስሳት መኖ ሣሮችን ተክለው እያለሙ መሆናቸውን ተናግረዋል። በየቀኑ የሚያገኙትን ከ200 ሊትር በላይ ወተት ለከተማው ማህበረሰብ በማቅረብ ገቢያቸውን እያሳደጉና ሀብት እያፈሩ መሆናቸውንም አስታውቀዋል፡፡ የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ምክትልና የዝርያ ማሻሻልና መኖ ልምት ዘርፍ ኃላፊ አደገ አለሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት፣ በክልሉ ከአዘርፉ የአርሶ አደሩንና የግል አልሚዎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ሲሰራ ቆይቷል። በተለይ በእንስሳት ዝርያ ማሻሻል፣ በመኖ አቅርቦት እና ጤና አጠባበቅ ሥራዎች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ አመርቂ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። የዝርያ ማሻሻል ሥራው በአምስት ዓመት ውስጥ ከአምስት እጥፍ በላይ ማደጉን ገልጸው፣ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 250 ሺህ የዳልጋ ከብቶችን ዝርያ ማሻሻል እንደተቻለ ገልጸዋል። በመኖ አቅርቦትና በእንስሳት ጤና አጠባበቅ ሥራም እንዲሁ ከፍተኛ ውጤት እንደተገኘ ያነሱት አደገ (ዶ/ር)፣ እነዚህ ተግባራት በወተት ምርትና ምርታማነት ላይ እመርታ ማምጣታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ቀደም ሲል በአካባቢው ሲመረት የነበረው ወተት ቤት ፍጆታ እንደማያልፍ አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ከአካባቢው አልፎ ለኢንዱስትሪዎች ማቅረብ የተቻለበት ደረጃ ላይ ተደርሷል ብለዋል። ለዚሀም ባለፈው በጀት ዓመት ከተመረተው 728 ሚሊዮን ሊትር ወተት 30 በመቶ የሚሆነውን ለኢንዱስትሪዎች መቅረቡን በማሳያነት ጠቅሰዋል። በተያዘው የ2019 በጀት ዓመትም ከ889 ሚሊዮን ሊትር በላይ ወተት ለማምረት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑንም አመልክተዋል፡፡
በድሬዳዋ ወደ ማምረት በተሸጋገሩ አዳዲስ አምራች ኢንዱስትሪዎች በተፈጠሩ የሥራ ዕድሎች ተጠቃሚ ሆነናል-ወጣቶች
Aug 13, 2026 96
ድሬደዋ፣ ነሐሴ 7/2018(ኢዜአ) በድሬዳዋ በ''ኢትዮጵያ ታምርት'' ንቅናቄ ወደ ማምረት በተሸጋገሩ አዳዲስ አምራች ኢንዱስትሪዎች በተፈጠሩ የሥራ ዕድሎች ተጠቃሚ መሆናቸውን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የከተማዋ ወጣቶች ገለጹ። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የሚታዩ የአሰራር ማነቆዎችን በመፍታት የአገር ውስጥ የማምረት አቅምን ለማሳደግ ዘመናዊ እና ውጤታማ ምህዳር መፍጠር አስችሏል። በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ንቅናቄው አምራቾች በሙሉ አቅማቸው እንዲያመርቱ ለማስቻል፣ የኃይል፣ የፋይናንስ፣ የመሬት እና የግብዓት አቅርቦት ጥያቄያቸውን ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመቀናጀት ፈጣን ምላሽ እንዲያገኝ አድርጓል። ይህም በርካታ አዳዲስና ነባር ፋብሪካዎች ግንባታቸውንና ማስፋፊያቸውን በፍጥነት አጠናቀው ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ ያስቻለ ሲሆን፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በአገር ውስጥ በመተካት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬን ማዳን አስችሏል። እንዲሁም ለበርካታ ዜጎች፣ በተለይም ለወጣቶች፣ ቋሚና አስተማማኝ የሥራ ዕድል እንዲፈጠር ትልቅ አስተዋጽኦን አበርክቷል። አስተየየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ወጣቶችም፤ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ድጋፍ እና ክትትል ወደ ማምረት በገቡ አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች በተፈጠሩ የሥራ ዕድሎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው የዩኒቨርስቲ ተመራቂዎች መካከል ወጣት አሸናፊ አስናቀ እና ወጣት ዱርሲቱ ሁሴን፤ በተፈጠረላቸው የስራ ዕድል ተጠቅመው ህይወታቸውን እየለወጡና ተጨማሪ ትምህርት እየተማሩ መሆኑን አንስተዋል። በኡርጂ ሳሙና ፋብሪካ በማሽን ኦፕሬተርነት ተቀጥረው የተሻለ ገቢ ማግኘት እንደቻሉ የተናገሩት ደግሞ ወጣት ኤሊያስ ሐሰን እና ወጣት ኢብሳ አሊ ናቸው። የፋብሪካ ባለቤቶችና የስራ አመራሮች በበኩላቸው ፋብሪካዎቹ በሙሉ አቅም ወደ ምርት ሲገቡ ተጨማሪ የስራ ዕድል እንደሚፈጥሩም ገልጸዋል። የአሜን የካርቶን ፋብሪካ ባለቤት አቶ ብሩክ በቀለ በበኩላቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ ባደረገላቸው ድጋፍ በ62 ሚሊዮን ብር ካፒታል በአንድ ዓመት ግንባታ አጠናቀው ማምረት መጀመራቸውን ተናግረዋል። የፋብሪካው ወደ ስራ መግባት ለ27 ሰዎች ቋሚ የስራ ዕድል በመፍጠሩና ከውጭ የሚገባን ምርት ማስቀረቱን ጠቁመዋል። የፋብሪካው ምርት ጥራቱን የጠበቀ ከመሆኑም በላይ ከፕላስቲክ የጸዳች ድሬዳዋን ለመፍጠር የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ጠቁመዋል። የኡርጂ ሳሙና ፋብሪካ ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ሐምዲያ ዑመር በበኩላቸው የድሬዳዋ አስተዳደር ለፕሮጀክት ማስፋፊያ መሬት፣ ለፋይናንስ እና ለኤሌክትሪክ ሀይል አቅርቦት ጥያቄቸው ፈጣን ምላሽ እንደሰጣቸው ተናግረዋል። ይህም በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ግንባታቸውን አጠናቀው ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ማስቻሉን ገልጸው ለ46 ሰዎች የስራ ዕድል መፍጠራቸውንም አስረድተዋል። የተለያዩ የውሃ ማጠራቀሚያ (ሮቶ) ምርቶቹን ወደ ጅቡቲ እና ሀርጌሳ ከተሞች በመላክ የውጭ ምንዛሬ እያስገኘ ያለው አሽራፍ የፕላስቲክ ፋብሪካ ስራ አስኪያጅ አቶ ሙሉጌታ ንጉሴ ፋብሪካው ለ40 ወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። አስተዳደሩ ለማምረቻ ቦታ ጥያቄያቸው ፈጣን ምላሽ በመስጠቱ በቀጣይ የተሻለ ስራ ለመስራት እንደተነሳሱም ገልጸዋል።
የግብርና ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ ከ559 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ተገኘ
Aug 13, 2026 108
ባህር ዳር ፤ነሐሴ7/2018 (ኢዜአ)፡- ከአማራ ክልል የቅባትና ጥራጥሬ ምርቶችን ለውጭ ገበያ በማቅረብ ከ559 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ገቢ መገኘቱን የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የሰብልና የኢንዱስትሪ ምርቶች ግብይት ዳይሬክተር አቶ ልንገረው አበሻ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከ5 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች ወደ ውጭ ተልከዋል። ወደ ተለያዩ ሀገራት ከተላኩት የግብርና ምርቶች ውስጥ ከ1 ሚሊዮን 942 ሺህ ኩንታል በላይ ሰሊጥና ኑግ እንደሚገኙበት የገለጹት ዳይሬክተሩ፤ ቀሪው ደግሞ የቦሎቄ፣ የአኩሪ አተር፣ የማሾና የቡና ምርቶች መሆናቸውን አመልክተዋል። በበጀት ዓመቱ ወደ ውጭ ከተላኩ የቅባት፣ የጥራጥሬና የቡና ምርቶች በአጠቃላይ ከ559 ሚሊዮን 880 ሺህ 84 የአሜሪካ ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱንም ተናግረዋል። ምርቶቹ ከተላኩባቸው ዋና ዋና አካባቢዎች መካከል አውሮፓ፣ መካከለኛው ምስራቅ፣ ህንድ፣ ሩቅ ምስራቅ እና የእስያ ሀገራት እንደሚገኙበት ጠቁመዋል። በአዲሱ የበጀት ዓመትም የተሻለ ምርት በጥራትና በብዛት አምርቶ ለውጭ ገበያ በማቅረብ ከዘርፉ የሚገኘውን የውጭ ምንዛሬ ገቢ ለማሳደግ ከባለድርሻ አካላት ጋር እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። በ2016/2017 የበጀት ዓመት ከክልሉ ከ6 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የቅባትና የጥራጥሬ ምርቶች ወደ ተለያዩ ሀገራት መላካቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በመኸር እርሻው ከ916ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ተሸፍኗል
Aug 13, 2026 176
አምቦ ፤ ነሐሴ 7/2018(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን በዘንድሮው የመኸር ወቅት ከ916 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መሸፈኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። ምዕራብ ሸዋ ዞን በኦሮሚያ ክልል ከሚገኙ ዋና ዋና እና ምርታማ የግብርና አካባቢዎች አንዱ ነው። አብዛኛው የዞኑ መሬት ለግብርና ተስማሚ የሆነ ወይናደጋ እና ደጋማ የአየር ጠባይ ያለው ሲሆን፣ አካባቢው በዋናነት በጤፍ፣ ስንዴ፣ ገብስ፣ በቆሎ፣ ማሽላ እንዲሁም በጥራጥሬና ቅባት እህሎች አምራችነቱ ይታወቃል። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ ደጀኔ ደቡሼ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን 902 ሺህ 892 ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ ከእቅድ በላይ 916ሺህ 735 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር ተሸፍኗል። ከለማው መሬት ከ34 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይሰበሰባል ተብሎም ይጠበቃል ብለዋል፡፡ የምርት እቅዱን ለማሳካትም ግብዓት መጠቀም፣ ደጋግሞ ማረስ፣ በመስመር መዝራት እና አረምን መከላከል ላይ ትኩረት መሰጠቱን አንስተዋል። ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰጠው ትኩረት አብዛኛው ሰብል በኩታ ገጠም የተዘራ እንደሆነ ገልጸው፤ በልማቱ ከ344 ሺህ በላይ አርሶአደሮች ተሳትፈዋል ብለዋል፡፡ የግብርና ባለሙያዎችም አርሶ አደሩ የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴን እና ሌሎች የተሻሻሉ አሰራሮችን እንዲሁም ግብአትን ተጠቅመው በመዝራት ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ ድጋፍ እያደረጉ እንደሚገኙም ነው አቶ ደጀኔ የተናገሩት፡፡ በዘር ከተሸፈነው ውስጥ ቀድመው የተዘሩ ሰብሎች አሁን ላይ በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በዞኑ የአምቦ ወረዳ አርሶ አደር ሙለታ ጉተማ፤ በመኸር እርሻ ወቅት ተገቢውን ምርት ለማግኘት አንድ ሄክታር ማሳቸውን ደጋግመው በማረስ በስንዴና በገብስ ሰብል መሸፈናቸውን ተናግረዋል፡፡ በግብርና ባለሙያዎች የሚሰጡ አሰራሮችንና ግብዓቶችን በመጠቀም ጥሩ ምርት ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል። በበጋ መስኖ ያለሙትን ምርት ሙሉ በሙሉ በማንሳት ወደ መኸሩ እርሻ ስራ መግባታቸውን የተናገሩት ደግሞ የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አርሶአደር አበራ ቶለሳ ናቸው። የተፈጥሮ ማዳበሪያንና ሰው ሰራሽ የአፈር ማዳበሪያ ተጠቅመው ሁለት ሄክታር መሬት በቆሎ፣ ማሽላ እና ስንዴ ዘር መሸፈናቸውንም ገልጸዋል። አርሶአደሮቹ በአሁኑ የመኸር እርሻቸውን አከናውነው የመንከባከብ ስራ እየሰሩ ይገኛሉ። በዞኑ ባለፈው መኸር ከለማው ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ 33 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት መገኘቱን ከዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የአፍሪካ አቪዬሽን አርማ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተቋማዊ ልህቀት በዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ዓይን
Aug 12, 2026 288
በሙሴ መለሰ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ የአንድን ሀገር ኢኮኖሚያዊ ትስስር፣ የቱሪዝም ዕድገት እና የጂኦፖለቲካዊ ተፅዕኖ የመወሰን ከፍተኛ አቅም ያለው ስትራቴጂካዊ ዘርፍ ነው። በአፍሪካ አህጉር በርካታ ሀገራት ብሔራዊ አየር መንገዶቻቸውን በትክክለኛ የንግድ መስመርና ጠንካራ ተቋማዊ መዋቅር ለመገንባት በሚታገሉበት በዚህ ወቅት፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ያሳየው ዘላቂ ዕድገትና ስኬት በመላው ዓለም ትልቅ አድናቆትንና ትኩረትን የሳበ አጋጣሚ ሆኗል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተመሠረተበትን 80ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በሚያከብርበት በዚህ ወቅት፣ ከትራንስፖርት ተቋም ከመሆን አልፎ የአፍሪካ አቪዬሽን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ መሪ በመሆን ቁልፍ ሚናውን አጠናክሮ ቀጥሏል። ተቋሙ በተከተለው የረጅም ጊዜ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ፣ በሙያዊ አስተዳደር እና ባደራጀው ዘመናዊ የአቪዬሽን ማዕከል አማካኝነት ሀገሪቱን የአህጉሪቱ ዋነኛ አገናኝ ድልድይ እና የትራንዚት መዳረሻ ሆኗል። ይህን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የላቀ ደረጃ የበለጠ ለማጠናከር እና የወደፊቱን የዓለም አቪዬሽን ፍላጎት ታሳቢ ያደረገው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ፕሮጀክት፣ ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ዘርፍ ያላትን የመሪነት ሚና ወደ አዲስ ምዕራፍ የሚያሸጋግር ግዙፍ መሠረተ ልማት ነው። ከአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት ላይ እየተገነባ የሚገኘው ይህ ሜጋ ኤርፖርት፣ የቦሌ ዓለም አቀፍ አየር መንገድን የጭነትና የመንገደኞች ጫና በመቀነስ በዓመት እስከ 110 ሚሊዮን መንገደኞችን ለማስተናገድ አልሞ የተነሳ ነው። ይህም ፕሮጀክት ሲጠናቀቅ በአፍሪካ ግዙፉ የአቪዬሽን ማዕከል በመሆን የቀጣናውን የቱሪዝም፣ የንግድና የሎጂስቲክስ እንቅስቃሴ በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያነቃቃው ይጠበቃል። ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን በሰሞኑ ዘገባቸው የኢትዮጵያ አየር መንገድን ስኬት እና የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ፕሮጀክት ግንባታ ላይ ትኩረታቸውን አድርገዋል። የዩናይትድ ኪንግደሙ ዕለታዊ ጋዜጣ ዴይሊ ኤክስፕረስ (Daily Express) በዘገባው እንደጠቀሰው፣ ከአዲስ አበባ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገነባው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ በዓለም አቀፉ የዛሃ ሀዲድ አርክቴክቶች ዲዛይን የተደረገ ግዙፍ ፕሮጀክት እንደሆነ አመልክቷል። አየር ማረፊያው እ.አ.አ. በ2030 በሚጠናቀቀው የመጀመሪያው ምዕራፍ 60 ሚሊዮን መንገደኞችን የማስተናገድ አቅም የሚኖረው ሲሆን፣ ይህም በዓመት 28 ሚሊዮን የሚያስተናግደውን የደቡብ አፍሪካውን ኦሊቨር ታምቦ እና 26 ሚሊዮን የሚያስተናግደውን የግብፁን ካይሮ ኤርፖርቶች በከፍተኛ ልዩነት በመብለጥ በአህጉሪቱ የመሪነቱን ቦታ እንደሚይዝ ገልጿል። ፕሮጀክቱ አራት የመሬት ላይ የአውሮፕላን መነሻና ማረፊያ መንገዶችን፣ የ38 ኪሎ ሜትር ፈጣን የባቡር መስመር፣ የሆቴልና የንግድ ማዕከላትን ያካተተ በመሆኑ፣ የዓለም ኃያላን አገራትን፣ አሜሪካንና ቻይናን ጨምሮ፣ የዓለም አቀፍ ኢንቨስተሮችን ትኩረት መሳቡን ዘገባው አመልክቷል። ሌላኛው የዩናይትድ ኪንግደም ዕለታዊ ጋዜጣ ዴይሊ ሚረር (Daily Mirror) የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስኬት በኤርፖርት መሠረተ ልማት ግንባታ ላይ ብቻ የተገደበ ሳይሆን፣ በተቋማዊ የአመራር ዘዴው ለአህጉሪቱና ለሌሎች ሀገራት ትልቅ ተሞክሮ እንደሆነ ገልጿል። ዲፕሎማት ካና ካናናታን በጋዜጣው ላይ ባሰፈረው ጽሑፍ፣ አየር መንገዱ በመንግሥት ሥር ሆኖ ሳለ እ.አ.አ. በ2025/26 በጀት ዓመት 9.1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማስገኘቱ፣ 20.7 ሚሊዮን መንገደኞችን ማጓጓዙ እና በ174 አውሮፕላኖች ወደ 150 ዓለም አቀፍ መዳረሻዎች መብረሩ “የመንግሥት ባለቤትነት የኪሳራ መንስኤ ነው” የሚለውን የተሳሳተ አመለካከት ያፈረሰ መሆኑን አመልክቷል። እንደ ስሪላንካ ያሉ ሀገራት በየዓመቱ ብሔራዊ አየር መንገዶቻቸውን ከመንግሥት ግምጃ ቤት ለመደጎም ሲታገሉ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግን ከፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ነፃ በሆነ የንግድ ስትራቴጂ መመራቱ የስኬቱ ምሥጢር መሆኑ ተመላክቷል። የኢትዮጵያ የአቪዬሽን አመራር ልህቀት ዓለም አቀፍ ተቀባይነት እያደገ መምጣቱ በጽሑፉ ላይ ሰፍሯል። በተመሳሳይ መልኩ ዘ ኢስት አፍሪካን (The East African) ላይ በቻርልስ ኦንያንጎ-ኦቦ የቀረበው ጽሑፍ እንደሚያስረዳው፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበላይነት የመጣው በጠንካራ የቴክኒክ ሥልጠና፣ በአውሮፕላን ጥገና ልህቀት፣ በረጅም ጊዜ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ፣ በተቋማዊ አሠራር እና በጠንካራ ዲሲፕሊን የሚመራ በመሆኑ ነው። አየር መንገዱ የራሱን ስኬት ከማስመዝገብ ባለፈ፣ የቀድሞና የአሁኑ አመራሮቹን እንደ ASKY፣ Malawi Airlines፣ Air Congo፣ Zambia Airways፣ Uganda Airlines እና RwandAir ባሉ በርካታ የአፍሪካ አየር መንገዶች ውስጥ በቁልፍ የካፒቴንነትና የአመራር ቦታዎች ላይ በመመደብ የመላው አፍሪካ አቪዬሽን አቅም እንዲገነባ መሠረት መሆኑን ጽሑፉ አመልክቷል። ታይምስ ኩዌት (The Times Kuwait) ባወጣው መረጃ መሠረት፣ እ.አ.አ. 1945 የተመሠረተው ይህ አየር መንገድ የ80 ዓመታት የልህቀት ጉዞውን በሚያከብርበት በዚህ ወቅት በስካይትራክስ (SKYTRAX) ዘንድ ለስምንት ተከታታይ ዓመታት “የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ” በመባል መመረጡን ገልጿል። አየር መንገዱ አዲስ አበባን የትራንዚት ማዕከል በማድረግ መንገደኞች በቆይታቸው እንደ እንጦጦ ፓርክ፣ አንድነት ፓርክ፣ ወንጪ ሐይቅ፣ ጨበራ ጩርጩራ፣ ላሊበላን እና የሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን ጨምሮ ሌሎች የመስብ ቦታዎችን እንዲጎበኙ በማስቻል የሀገሪቱን የቱሪዝም ዘርፍ እያነቃቃ እንደሚገኝ ጠቅሷል። በአጠቃላይ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስኬት የአንድ ሀገር ተቋም ጥንካሬ ማሳያ ብቻ ሳይሆን፣ የአፍሪካ አቪዬሽን ኢንዱስትሪ በሙያዊ አመራርና በረጅም ጊዜ ስትራቴጂካዊ ዕቅድ ከተመራ ምን ያህል ስኬታማ መሆን እንደሚችል ያሳየ ትልቅ ተሞክሮ ነው። በቢሾፍቱ እየተገነባ የሚገኘው አየር ማረፊያ ሲጠናቀቅ የመንገደኞችን የማስተናገድ ጫና በመቀነስ፣ የአህጉሪቱን የንግድ፣ የሎጂስቲክስና የቱሪዝም ትስስር ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋግረዋል። ይህ የራዕይና የተቋማዊ ጥንካሬ ቅንጅት ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የአቪዬሽን ካርታ ላይ ያላትን ተፅዕኖ ፈጣሪነት ይበልጥ የሚያጠናክረው ይሆናል።
በሸገር ከተማ በምግብ ራስን ለመቻል የሚያስችሉ የግብርና ስራዎች በመከናወን ላይ ናቸው
Aug 12, 2026 138
ሸገር ፤ነሐሴ 6/2018 (ኢዜአ)፡– በሸገር ከተማ ተረጂነትን ለማስወገድ እና በሀገር አቀፍ ደረጃ የተያዘውን በምግብ እህል ራስን የመቻል ዕቅድ ለማሳካት የሚያስችሉ የግብርና ስራዎች በመከናወን ላይ መሆናቸውን የከተማዋ አስተዳደር አስታወቀ። ኢትዮጵያ በምግብ እህል ራስን ለመቻል እና የስንዴ ምርትን ከውጭ ማስገባትን ለማስቆም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በስፋት እየተገበረችው የሚገኘው የኩታገጠም እርሻ ውጤት እያስገኘ ነው። የሸገር ከተማ አስተዳደርም በከተማ ዙሪያ የሚገኙ የእርሻ መሬቶችን በዘመናዊ አሰራር በማልማት ተረጂነትን ለማስወገድ እና የከተማዋን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል። በከተማዋ ኩራ ጂዳ ክፍለ ከተማ በ340 ሄክታር መሬት ላይ በኩታገጠም አሰራር ለምርጥ የስንዴ ዘር ብዜት የሚሆን የዘር መዝራት ስራ ዛሬ ተከናውኗል። ይህን ዓላማ ለማሳካት ዋናው ማነቆ የሆነውን የምርጥ ዘር እጥረት ለመቅረፍ፣ ዛሬ በኩራ ጂዳ ክፍለ ከተማ የተካሄደው የ340 ሄክታር መሬት ኩታገጠም ዘመቻ ጥራት ያለው የስንዴ ዘር በማባዛት ለአካባቢውና ለሌሎች አራሾች ለማቅረብ ያለመ ነው። በስነ-ስርዓቱ ላይ የተገኙት በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሸገር ከተማ የግብርና እና ልማት ክላስተር አስተባባሪ አቶ ግርማ ሀይሉ እንደገለጹት፤ በከተማዋ ምርታማነትን በማሳደግ በግብርናው ዘርፍ የሥራ ዕድል ለመፍጠር የሚያስችሉ ተግባራት በሰፊው በመከናወን ላይ ይገኛሉ። በተለይም በከተማዋ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ፣ የውጭ ኤክስፖርትን ማሳደግ እና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን የመተካት ዕቅዶችን ለማሳካት በትኩረት እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም ለከተማዋ አርሶ አደሮች የክህሎት ሥልጠና በመስጠት የሥራ ባህልን መለወጥ ተችሏል ብለዋል። ዛሬ የተካሄደው ስንዴን በኩታ ገጠም ማሳን በዘር የመሸፈን ዘመቻም የዚሁ ጥረት አካል መሆኑን ጠቁመዋል። የዛሬው ስንዴን የመዝራት ዘመቻ የግብርና ምርታማነትን የሚያሳድጉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በሙሉ በመጠቀም የተከናወነ መሆኑን አብራርተዋል። በዚሁ መሠረት በከተማዋ በዘንድሮው የመኸር እርሻ ወቅት 70 ሺህ ሄክታር መሬት በኩታገጠም ለማልማት ታቅዶ እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። የሸገር ከተማ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ደጀኔ በቀለ በበኩላቸው፤ በከተማዋ የምርት እና የምርታማነት መጠንን ለማሳደግ ዘንድሮ እየተከናወነ ካለው የግብርና ሥራ ውስጥ እስካሁን 55 በመቶ የሚሆነው ሙሉ የግብርና ፓኬጅ በመጠቀም እንዲለማ መደረጉን ገልጸዋል። በከተማዋ የኩራ ጂዳ ክፍለ ከተማ አስተዳዳሪ አቶ ተማም ሁሴን፤ በክፍለ ከተማው እየለማ ካለው አጠቃላይ መሬት ውስጥ ስንዴ በኩታገጠም የማልማቱ ስራ ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል። የኩታገጠም እርሻ የምርት ማሳደጊያ ግብዓቶችን በቀላሉ እንዲያገኙ ከማስቻሉም በላይ ምርትና ምርታማነታቸውን እንዳሳደገላቸው የተናገሩት ደግሞ በዘር ብዜቱ ተሳታፊ አርሶ አደሮች ናቸው።