ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የግብርና ምርት እሴት ሰንሰለትን ለማሻሻል ትብብርና የፖሊሲ ማዕቀፍ መተግበር ይገባል - ኢጋድ
Sep 15, 2026 354
አዲስ አበባ፤ መስከረም 5/2019 (ኢዜአ)፡- በአባል ሀገራት ቀጣና የግብርና ምርትን ለማሻሻልና እሴት ለመጨመር ትብብርን በማጠናከርና ሊያግባባ የሚችል የጋራ የፖሊሲ ማዕቀፍ መተግበር እንደሚገባ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ገለጸ። ኢጋድ እንደ አውሮፓውያን የዘመን አቆጣጠር ከ2026 እስከ 2035 ለ10 ዓመታት የሚተገብረውን የቀጣናው የግብርና ምርት የምግብ ሥርዓት ኢንቨስትመንት ዕቅድ የባለሙያዎች ግምገማና በሚኒስትሮች የማጽደቅ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ እያካሄደ ነው። የኢጋድ የምግብ ሥርዓት ግንባታ አቅም ፕሮግራም አስተባባሪ ሰናይት ረጋሳ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኢጋድ ቀጣና ሀገራት እንደ ጎርፍ፣ ድርቅና መሰል የተፈጥሮ አደጋዎችን በተደጋጋሚ የሚያስተናግዱ ናቸው። የአፍሪካ መሪዎች እ.ኤ.አ. በ2025 በዩጋንዳ ካምፓላ ተገናኝተው የምግብ ሥርዓት ግንባታ አቅም ስምምነት ሰነድ በመፈራረም ለትግበራው ቁርጠኝነታቸውን ማሳየታቸውን አስታውሰዋል።   በዚህም በአህጉር፣ በቀጣናና በሀገር ደረጃ ገቢራዊ ለማድረግ እንቅስቃሴ መደረጉን ገልጸው፤ የኢጋድ የግብርና ምርት የምግብ ሥርዓት ኢንቨስትመንት የ10 ዓመት ዕቅድ የዚሁ አካል መሆኑን ተናግረዋል። ከምግብ ዋስትና ጋር የተያያዙ ችግሮች በሀገር ደረጃ ብቻ የሚፈቱ አለመሆናቸውን ገልጸው፤ የ10 ዓመት ዕቅዱ የሀገራትን የጋራ ትብብር እንደሚያጠናክር ብለዋል። ለአብነት የበረሃ አንበጣ በቀጣናው ቢከሰት አንድ ሀገር ብቻውን የሚፈለገውን ውጤት ማምጣት አይችልም ያሉት አስተባባሪዋ፤ የቀጣናው ሀገራት በጋራ ጉዳዮች ላይ የጋራ መፍትሔና እርምጃ መውሰድ የሚችሉበትን ዕድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ዕቅዱ ሀገራት በተናጠል ከራሳቸው ነባራዊ ሁኔታ በመነሳት ከሚወስዷቸው የመፍትሔ አማራጮች ባለፈ ትብብራቸውን ማጠናከርና የዕውቀት ሽግግር መፍጠር እንደሚያስችልም ተናግረዋል። የኢጋድ የግብርና ምርት የምግብ ሥርዓት ኢንቨስትመንት ዕቅድ የግብርና ምርትን ከማሳደግ ባለፈ እሴት መጨመር የሚቻልበትን አቅም መገንባት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።   ድርቅ በሚከሰትበት ወቅት ቅድመ ማስጠንቀቂያ መስጠት፣ የሴቶችን ተሳትፎ ማሳደግ፣ ድንበር ተሻጋሪ በሽታዎችን በጋራ መከላከል የሚችሉበት ሥርዓት እንዲዘረጋ ድጋፍ ማድረግ ያስችላል ብለዋል። ከዚህም ባለፈ የቀጣናው ሀገራት የሚስማሙበትን እና ግብራዊ ሊያደርጉት የሚችለውን የጋራ ቀጣናዊ የፖሊሲ ማዕቀፍ እንዲኖራቸው የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ሚኒስትር ከፍተኛ አማካሪና የአፍሪካ ልማት ፕሮግራም ተወካይ ዜና ሀብተወልድ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከአፍሪካና ከቀጣናው ሀገራት ጋር የተናበበ ዕቅድ በመተግበር በአርዓያነት የሚጠቀስ ውጤት አስመዝግባለች ብለዋል። በሌማት ትሩፋት፣ በስንዴ ልማት እንዲሁም አሁን በስፋት ግብራዊ በተደረገው የሩዝ ልማት ተጨባጭ ለውጥ መገኘቱን ገልጸዋል። ግብርና የአፍሪካ የልማት ሞተር መሆኑን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ ይሄንን ታሳቢ ያደረገ የግብርና ዕመርታ አምጥታለች ብለዋል። በቀጣይም ኢትዮጵያ በካምፓላ ስምምነትና በኢጋድ የ10 ዓመት የኢንቨስትመንት ዕቅድ ላይ በመመስረት የቀጣይ 10 ዓመት የተናበበ ዕቅድ በማውጣት ግብራዊ እንደምታደርግ ገልጸዋል። ኢጋድ ኢትዮጵያን ጨምሮ ለቀጣናው ሀገራት የምግብ ዋስትና መረጋገጥና በሽታ መከላከል ሥርዓት ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸው፤ ቀጣናዊ ትብብርና ተቋማዊ አንድነትን ማጠናከር ይገባል ብለዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስትራቴጂካዊ አቅምና ሙያዊ ብቃት ለመላው አፍሪካ አርአያ የሚሆን ነው 
Sep 15, 2026 299
አዲስ አበባ፤ መስከረም 5/2019 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፉት አስርት ዓመታት የገነባው ስትራቴጂካዊ ዲሲፕሊን፣የቴክኒክ ልህቀት እና የላቀ ሙያዊ የብቃት ደረጃ ለመላው አፍሪካ አርአያ የሚሆን ነው ሲሉ የቀድሞ የአሜሪካ የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ሚኒስትር ቲቦር ናጊ ገለጹ። የአየር መንገዱ ስኬት በመንግስት ባለቤትነት ብቻ የተወሰነ ሳይሆን በሙያዊ ስነምግባርና በገለልተኝነት በመመራቱ ጭምር መሆኑን የቀድሞው ዲፕሎማት ከፐልስ ኦፍ አፍሪካ ጋር ባደረጉት ቆይታ ተናግረዋል። ተቋሙ በቴክኒክ አቅምና በሰው ኃይል ልማት ላይ ያደረገው ሰፊ ኢንቨስትመንት አሁን ላይ ለደረሰበት ዝና እና ስኬት ቁልፍ ሚና መጫወቱን አመልክተዋል።   አየር መንገዱ ጠንካራ ስትራቴጂ ያለው እና የላቀ የቴክኒክ አቅም የተጎናጸፈ መሆኑን ገልጸው የአውሮፓ አየር መንገዶች አብራሪዎቻቸውን በአዲስ አበባ በሚገኙ ማሰልጠኛዎች (ሲሚውሌተር) ልምምድ እንዲያደርጉ እንደሚልኩ አንስተዋል። የተቋሙ መካኒኮችም በዓለም ምርጥ ከሆኑት ተርታ እንደሚመደቡ ጠቅሰው መንገደኞች ሁልጊዜም የኢትዮጵያ አየር መንገድን ተመራጭ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል። ዓለም አቀፍ በረራዎች በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት ተቋርጠው በነበሩበት አስቸጋሪ ወቅት አየር መንገዱ የላቀ ሙያዊ ብቃት ማሳየቱን ናጊ አስታውሰዋል። በወቅቱ የቀድሞ የአሜሪካ የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ሚኒስትር ቲቦር ናጊ በሚያገለግሉበት ወቅት፣ ሌሎች አየር ማረፊያዎች በረራቸውን ባቋረጡበት ጊዜ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስራ መቀጠሉን ገልጸዋል። በዚህም ምክንያት አሜሪካ ዜጎቿን ከአፍሪካ ለማስወጣት አየር መንገዱን በስፋት ስትጠቀም እንደነበር በማውሳት የአየር መንገዱን ጽናትና አይበገሬነት አንስተዋል። የቢሾፍቱን ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ያደነቁ ሲሆን ኢትዮጵያ በአፍሪካ የኢኮኖሚና የአቪዬሽን መሪነት እንድትቀጥል ይህ ፕሮጀክት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።   የአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታ የረጅም ጊዜ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ አርቆ አሳቢነት የተሞላበት አካሄድ ነው ብለዋል። አዲስ አበባ እጅግ ከፍ ያለ ቦታ ላይ መሆኗ ለአንዳንድ አውሮፕላኖች ማረፍና መነሳት አስቸጋሪ መሆኑን በመጥቀስ፣ ይህም የፕሮጀክቱን ስትራቴጂካዊ ፋይዳ የጎላ የሚያደርገው መሆኑን ተናግረዋል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ፕሮጀክት 12.5 ቢሊዮን ዶላር የሚፈጅ ሲሆን፤ ይህ ሜጋ ፕሮጀክት በቢሾፍቱ ከተማ እየተገነባ ይገኛል። ፕሮጀክቱ ኢትዮጵያን ይበልጥ የአፍሪካ ግዙፍ የአቪዬሽን ማዕከል የሚያደርጋት ነው። የኢትዮጵያን አየር መንገድ ስኬት ከረጅም ጊዜ የተቋም ጽናትና ኢንቨስትመንት ጋር የሚቆራኝ ነው ብለዋል። የቴክኒክ ባለሙያዎች ብቃት፣ስትራቴጂካዊ አስተዳደር እና የመሰረተ ልማት መቀናጀት እንዲሁም የሀገሪቱ ኢኮኖሚ እና የዓለም አቀፍ ትስስር እድገት አየር መንገዱ ያለውን አህጉራዊ ሚና ይበልጥ እንደሚያሳድገው አመልክተዋል።
የስንዴ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ አርሶ አደሩን ተጠቃሚ የሚያደርግ ፕሮጀክት ተግባራዊ እየተደረገ ነው
Sep 15, 2026 260
አዳማ፤ መስከረም 5/2019 (ኢዜአ) ፡- የስንዴ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያግዝ የስንዴ ልማት እሴት ሰንሰለት ፕሮጀክት ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ ለኢዜአ እንዳስታወቀው በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም የስንዴ ልማት እሴት ሰንሰለት ፕሮጀክት ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል። ፕሮጀክቱ የስንዴ ሰብሉ ድርቅን፣ ከፍተኛ ሙቀትን፣ ተባዮችንና ያልተጠበቀ የዝናብ መዛባትን የሚቋቋሙ የምርጥ ዘር ዝርያዎችን መጠቀም ላይ እንደሚያተኩርም ተገልጿል። በፕሮጀክቱ በስንዴ ልማቱ ላይ የሚካሄዱት የድጋፍና ክትትል ተግባራቱ በምርት ላይ ብቻ የተወሰኑ ሳይሆኑ ሙሉ የልማት የእሴት ሰንሰለቱን የሚያካትት መሆኑም እንዲሁ። ይህ አሰራር ለገበሬዎች ከዘርና ቴክኖሎጂ አቅርቦት ጀምሮ እስከ ሰብል ስብሰባ፣ ማከማቸት፣ ማቀናበርና ምርቱን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እስከ ማቅረብ ያሉትን ሙሉ ሂደቶች ያቃልላል ተብሏል። በአጠቃላይ ሀገሪቱ የአየር ንብረት ለውጥ በሚያመጣው ተጽዕኖ ሳትበገር የስንዴ ምርቷን በማሳደግ የምግብ ዋስትናዋን ለማረጋገጥና ወደ ውጭ የመላክ አቅሟን ለማጠናከር እያደረገች ያለችውን የተቀናጀ እንቅስቃሴ የሚደግፍ ፕሮጀክት መሆኑ ነው የተገለጸው። በግብርና ሚኒስቴር የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ አብዱልሰመድ አብዶ ለኢዜአ እንዳስታወቁት ፕሮጀክቱ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ ሶማሌ እና አፋር ክልሎች ነው። በዚህም በክልሎቹ የሚገኙ 76 ወረዳዎችና 1 ሺህ 129 ቀበሌዎችን በፕሮጀክቱ ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ለአምስት አመታት ተግባራዊ በሚደረገው በዚህ ፕሮጀክት በአካባቢዎቹ የስንዴ ምርትና ምርታማነትን በማሻሻል አነስተኛ ይዞታ ያላቸው ስንዴ አምራች አርሶ አደሮችን ገቢ ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህ ረገድ እየተከናወኑ ካሉ ስራዎች መካከል የዘር ግብዓት አቅርቦት ዋነኛው መሆኑን ጠቅሰው ለዚህም በየደረጃው ከሚገኙ የግብርና ምርምር ተቋማት ጋር በመቀናጀት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ፕሮጀክቱ ተግባራዊ በተደረገባቸው ባለፉት ሁለት አመታት ውስጥ የዳቦና የመኮሮኒ ስንዴ ዘርን በጥራት በማምረት በፕሮጀክቱ ለታቀፉ አርሶ አደሮች ማሰራጨት መቻሉን ገልጸዋል። ይህም የመነሻ ዘር አቅርቦት ከማሻሻል ባለፈ የስንዴ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ማስቻሉን አመላክተዋል። ፕሮጀክቱ ከአፈር ለምነትና ጤንነት ጋር ተያይዞ ስንዴ አምራች በሆኑ አካባቢዎች እያጋጠመ ያለውን ሰፊ የአሲዳማነት ችግርንም ለማቃለል ትኩረት መስጠቱን አስተባባሪው አስታውቀዋል። በዚህ ረገድ ስለ ኖራ አጠቃቀም ለአርሶ አደሩ በሰርቶ ማሳያ በማሳየት በአሲዳማነት የተጠቃ አፈርን በማከም ምርታማነት እንዲሻሻል በፕሮጀክቱ ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የኖራ አቅርቦትን በዘላቂነት ለማረጋገጥ በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ትላልቅ የኖራ ወፍጮዎች እየተተከሉ ሲሆን፣ ለአፈር ለምነት የሚያግዙ ቴክኖሎጂዎችን የማስተዋወቅ ስራም ተያይዞ እየተከናወነ ነው ብለዋል። ለመስኖ ልማት አመቺ በሆኑ አካባቢዎች የ18 የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተፋጠነ እንደሚገኝ የጠቆሙት ኃላፊው፣ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሜካናይዜሽን ማዕከላትን ከመገንባት ጎን ለጎን በአራቱ ክልሎች 49 ትላልቅና መካከለኛ የስንዴ ማከማቻ መጋዘኖችን የመገንባት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። ከአፍሪካ ልማት ባንክ በተገኘ 94 ነጥብ 3 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው ይህ ፕሮጀክት፣ መንግሥት የስንዴን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ለያዘው ስትራቴጂ ስኬታማነት ወሳኝ ድርሻ አለው ብለዋል።    
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የጥራት ደረጃውን የጠበቀ ቡና በብዛት ለማዕከላዊ ገበያ ይቀርባል
Sep 14, 2026 349
ዲላ፣ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በተያዘው በጀት አመት ቡናን በጥራት እና በብዛት አዘጋጅቶ ለማእከላዊ ገበያ ለማቅረብ ከወዲሁ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ቡናና ቅመማ ቅመም ባለሥልጣን ገለጸ። ክልላዊ የቡና ምርት አሰባሰብና ተጓዷኝ ተግባራት ላይ የባለድርሻ አካላት የውይይት መድረክ ዛሬ በዲላ ከተማ ተካሂዷል።   የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ አማኑኤል ብሩ በወቅቱ እንዳሉት በክልሉ የቡና አመራረትና ዝግጅት እየተሻሻለ በመምጣቱ ምርታማነትና ጥራትን ማሳደግ ተችሏል። ከክልሉ በተያዘው 2019 በጀት አመት ቡናን በጥራት በማዘጋጀት በብዛት ለማእከላዊ ገበያ ለማቅረብ በየደረጃው በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በበጀት አመቱ ከ48 ሺህ ቶን በላይ ቡና ለማእከላዊ ገበያ እንደሚቀርብ አመላክተዋል። ጥራት ላለው ቡና የተሻለ ዋጋ መቆረጡ የዘርፉን ተወዳዳሪነት አሳድጓል ያሉት ደግሞ የጌዴኦ ዞን የቡና ላኪዎች ማህበር ሰብሳቢ አቶ ኢያሱ ወራሳ ናቸው።   ባለፈው ዓመት ቡናን በጥራት ከማዘጋጀት ባለፈ በጊዜ ለገበያ እንዲቀርብ መደረጉ ተጠቃሚነታችን እንዲረጋገጥ አስችሏል ብለዋል፡፡ በተያዘው ምርት ዘመንም ጥራት ያለው ቡና ለገበያ ለማቅረብ ከወዲሁ ዝግጅት ማጠናቀቃቸውን አመልክተዋል። ቡና ላኪ አርሶ አደር አሰለፈች ጋን በበኩላቸው የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማነትን ማሳደግ መቻላቸውን ተናግረዋል። በተያዘው ዓመትም ከማሳቸው የሚያገኙትን የቡና ምርት በጥራት በማዘጋጀት በቀጥታ የገበያ ትስስር ለውጭ ገበያ ለማቅረብ እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በመድረኩ አምራቾች፣ ላኪ አርሶ አደሮች፣ አቅራቢ ነጋዴዎችና ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።    
​በዞኖቹ በሰላም እንዲሁም በማህበራዊና ኢኮኖሚ ዘርፎች የተገኙ ውጤቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Sep 14, 2026 280
​ወልድያና ደብረ ማርቆስ ፤ መስከረም 4/ 2019(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በሰሜን ወሎና ምስራቅ ጎጃም ዞኖች በተጠናቀቀው በጀት አመት በሰላም እንዲሁም በማህበራዊና ኢኮኖሚ ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተገኙ አበረታች ውጤቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገለጸ። በሰሜን ወሎና ምስራቅ ጎጃም ዞኖች "አርቆ ማየት፤ አልቆ መስራት" በሚል መሪ ሐሳብ የ2018 በጀት አመት የስራ አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት የዕቅድ ትውውቅ መድረክ ተካሂዷል።   የሰሜን ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አራጌ ይመር በመድረኩ ላይ እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ በሰላም እንዲሁም በማህበራዊና ኢኮኖሚ መስኮች አበረታች ውጤት ተመዝግቧል። በዞኑ የጸጥታ ሃይሉና በህብረተሰቡ የተቀናጀ ጥረት ሰላምን ዘላቂ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል ። በዚህም በመንግስት የቀረበውን የሰላም አማራጭ በመቀበል በርካታ የታጠቁ ኃይሎች መግባታቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል። በስራ እድል ፈጠራ በተከናወኑ ተግባራት ከ180 ሺህ በላይ የሚሆኑ ዜጎች በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዘርፎች መሰማራታቸውን ተናግረዋል። በበጋ መስኖ ልማት ከ231 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ ዘርፉ የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከቱን አንስተዋል ። በዲጂታላይዜሽን ትግበራም አበረታች ውጤት መመዝገቡን ጠቁመው በተያዘው 2019 በጀት አመት በየዘርፉ የተመዘገቡ ውጤቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል በትኩረት እንደሚሰራ አስታውቀዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የሰሜን ወሎ ዞን ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ወንድሙ በበኩላቸው የአመራሩን የማስፈጸም አቅም በመገንባት በልማትና መልካም አስተዳደር ስራዎች ላይ ለውጥ እንዲመጣ ተደርጓል ብለዋል። በዞኑ ከጉባላፍቶና ግዳን ወረዳዎች ነዋሪዎች መካከል አቶ ያለው ገደፋውና ወይዘሮ ደብረወርቅ ማዕረግ፤ እንደገለጹት መድረኩ በተጠናቀቀው በጀት አመት የታዩ ክፍተቶችን በማረም በተያዘው የበጀት ዓመት የተሻለ ለመፈጸም የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል። በተያያዘ ዜና የምስራቅ ጎጃም ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኑርልኝ ብርሃኑ እንደገለጹት በ2018 በጀት ዓመት ዞኑ በልማትና መልካም አስተዳደር ስኬቶች የተመዘገቡበት ነው ።   በበጀት ዓመቱ በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በኢንቨስትመንትና ሌሎች ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የላቀ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን አስረድተዋል። ዞኑ በበጀት አመቱ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎች በክልሉ ከሚገኙ ዞኖች ሶስተኛ ደረጃ ይዞ ማጠናቀቁ የዚሁ ማሳያ ነው ሲሉ አብራርተዋል። በተያዘው በጀት አመት በሁሉም ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አመላክተዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የምስራቅ ጎጃም ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ተስፋዬ በላይ በበኩላቸው በፓርቲው አመራር ሰጪነት በተከናወኑ የሰላምና የልማት ስራዎች ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል። በዞኖቹ በተካሄደው መድረክ ከዞን፣ ወረዳና የከተማ አስተዳደሮች የተወጣጡ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች እንዲሁም የህብረተሰብ ተወካዮች ተሳትፈዋል ።
የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም አጎልብቷል
Sep 14, 2026 367
አዲስ አበባ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር ዕድገትን በማፋጠን ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም ማጎልበቱን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶች ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር አዝጋሚና መዋቅራዊ የዕድገት ስብራትን በማከም፣ ዓለም አቀፍ ንግድና ኢንቨስትመንትን በማበራታታት በሁሉም ዘርፍ ዕድገትን እያሳለጠ ነው። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶች ለኢዜአ እንዳሉትም፤ የኢትየጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የብዝኅ ኢኮኖሚ ልማት ፍኖትን በማብሰር ዕድገት የሚያፋጥን እመርታዊ ውጤት እያስገኘ ነው። የኢኮኖሚ ዘርፎች እመርታዊ ውጤትም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ኢትዮጵያን ወደተሻለ የብልፅግና ምዕራፍ ማሸጋገር ያስቻሉ ጠንካራ መሰረቶችን እንደጣሉ ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አስራት አፀደወይን (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ግዙፍ ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም በማጎልበት አመርቂ ውጤት አስገኝቷል ብለዋል። የመደመር መንግሥት ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት የመፈጸም አቅም የትውልድን መሻት በመቅረጽ አኩሪ የአስተሳስብ ለውጥ የመጣባቸው መሆኑን አንስተዋል። ለአብነትም የመገጭ የመስኖና ንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክትን ጨምሮ ለበርካታ ዓመታት የሕዝብ የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ሆነው የቆዩ ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት የሚገነቡበትን ዕድል እንደፈጠረ ገልጸዋል። መንግሥት ለሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ የሰጠው ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥርም የከተማና ገጠር የልማት ውጤታማነትን በማሻሻል ኢትዮጵያን ተምሳሌት ሀገር እያደረጋት መሆኑን ተናግረዋል። የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ደረጄ እንግዳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የፖሊሲ እርምጃ ቀጣይነት ያለው ዕድገት እያስመዘገበ ነው ብለዋል።   የመደመር መንግሥት ዕድግትን በማፋጠን የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የሚታዩና የሚጨበጡ ውጤቶችን ማስገኘት እንደቻለ ጠቅሰዋል። የፖሊሲ እርምጃውም ኢትዮጵያ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር ታላቁ የሕዳሴ ግድብን ጨምሮ በከተማና ገጠር ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መፈጸም እንዳስቻላት አስረድተዋል። በተጨማሪም የጉባ ብስራት የሆኑትን እንደ ቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያና ሌሎች ግዙፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ አበርክቶ ያላቸው ዐበይት ፕሮጀክቶችን ማስጀመር እንዳስቻላት አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የተሰናሰለ የከተማና ገጠር ሁለንተናዊ የልማት ጉዞም አፍሪካዊት የብልፅግና ተምሳሌት ኢትዮጵያን ለቀጣዩ ትውልድ የሚያሻግር ታሪክ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።     በኢትዮጵያ በከተማና ገጠር በጥራትና ፍጥነት ተገንብተው የሚጠናቀቁ የልማት ፕሮጀክቶች የመንግሥትን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጡ ናቸው ያሉት ደግሞ የሰላሌ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፈየራ ዲንሳ (ዶ/ር) ናቸው። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የፖሊሲ እርምጃም ድኅነትና ኋላቀርነትን የሚገቱ የልማት ተነሳሽነቶችን በማስተግበር ሀገርን ወደ ተሻለ የዕድገት ምዕራፍ እያስፈነጠረ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ከነበረበት አደጋ ተላቆ ለምርቃት መብቃት በራስ መተማመን መንፈስን በማጎንጸፍ ተጨማሪ ግዙፍ ፕሮጀክቶች እንዲጀመሩ ማስቻሉን ተናግረዋል።   የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዑባህ አደም (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የልማት ስኬቶች የዜጎችን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ዕድገትን የሚያፋጥን አቅም መፍጠራቸውን ገልጸዋል። ለአብነትም የኢትዮጵያ ከተማና ገጠር የኮሪደር ልማት ውጤቶች የሀገርን ገጽታ በመገንባት አቅዶ የመፈጸም አቅምን ያጎለበቱ ውጤታማ የልማት ሥራዎች መሆናቸውን አንስተዋል። በቀጣይም ሀገር በቀል የፖሊሲ እርምጃዎች የፈጠሩትን ዕድል በመጠቀም መንግሥትና ሕዝብ የሀገርን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት ለማረጋገጠ በርብርብ መስራት እንደሚጠበቅ አስገንዝበዋል።
የህዝብን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት አጠናክሮ ለማስቀጠል ርብርብ ይደረጋል -አስተዳደሩ
Sep 14, 2026 128
መተማና ሰቆጣ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- የህዝብን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን በላቀ ቅንጅትና ትብብር ለማስቀጠል ርብርብ እንደሚደረግ ተጠቆመ። በምዕራብ ጎንደር ዞን እና በዋግ ህምራ ብሄረሰብ አስተዳደር የ2018 የበጀት ዓመት እቅድ አፈፃፀም እና የ2019 ዓ.ም እቅድ ትውውቅ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   የምዕራብ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ በገንዳ ውሃ ከተማ እየተካሄደ ባለው መድረክ እንዳሉት፤ ባለፈው የበጀት ዓመት በተደረጉ የተቀናጁ ጥረቶች አስተማማኝ ሰላም በመገንባት አበረታች ውጤት ተመዝግቧል። ለአካባቢው ሰላምና መረጋጋት መስፈን የህዝቡ ንቁ ተሳትፎና ያልተቋረጠ ድጋፍ ቁልፍ ሚና መጫወቱን ገልፀዋል። በበጀት ዓመቱ በግብርና ልማት፣ በገቢ አሰባሰብ፣ በከተማ ልማትና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተሻሉ አፈጻጸሞች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፤ የተገኙ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል በተሻለ መልኩ ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። የዞኑ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ እንዳለው ማሩ በበኩላቸው፤ ህዝቡ ከመንግስት ጎን በመቆም ላሳየው አበረታች የልማትና የሰላም ፍላጎት ምስጋና አቅርበዋል።   በ2019 የበጀት ዓመት የታቀዱ የልማትና የመልካም አስተዳደር ግቦችን ለማሳካት የፓርቲው አመራርና አባላት ህዝቡን በንቅናቄ በማሳተፍ በቁርጠኝነት እንደሚሰሩም ነው የተናገሩት። በተመሳሳይ በዋግ-ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር በ2019 በጀት ዓመት የአካባቢን ፀጋ መሰረት ያደረጉ እቅዶችን አቅምን አሟጦ ለመስራት ዝግጅት መደረጉን የገለፁት ደግሞ የሰቆጣ ከተማ ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዳግም ባይነሳኝ ናቸው።   በተጠናቀቀው ዓመት ውስብስብ ችግሮችን በመቋቋም በርካታ የልማት ስኬቶችን ማስመዝገብ መቻሉን አስታውሰው፤ በአዲሱ በጀት ዓመት የተመዘገቡ ስኬቶችን በላቀ ደረጃ ለመፈፀም የሚያስችል አሰራር መዘርጋቱን ተናግረዋል። የአመራሩን ቅንጅታዊ አሰራር ይበልጥ በማሳደግ ህዝብን ያሳተፉ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራትን ማስፋፋት የአዲሱ በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ገልፀዋል። በየደረጃው የሚገኙ አስፈፃሚዎችም ተጨባጭና ውጤታማ እቅድ በማቀድና በመፈፀም ለስኬቱ ሊረባረቡ እንደሚገባ አሳስበዋል። ለተከታታይ ሶስት ቀናት በሚካሄዱት መድረኮች የወረዳና ከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች ተሳታፊ ሆነዋል።  
በባህር ዳር ከተማ አስተማማኝ ሰላምና ተጨባጭ የልማት ስራዎችን ማከናወን ተችሏል
Sep 14, 2026 93
ባህር ዳር፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦ በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው አስታወቁ። «አርቆ ማየት፤ አልቆ መሥራት» በሚል መሪ ሐሳብ የመንግሥትና ፓርቲ የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት የዕቅድ ትውውቅ መድረክ መካሄድ ጀምሯል።   ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው በዚሁ መድረክ እንደገለጹት፤ በከተማዋ የፀጥታ አካላትና በሕዝቡ ጠንካራ ቅንጅት አስተማማኝ ሰላምን ማስፈን ተችሏል። ባህር ዳርን ውብ፣ ጽዱ እና አረንጓዴ የማድረግ ተግባር በተጨባጭ እውን ማድረግ መቻሉንና የመሠረተ ልማት ግንባታዎች የከተማዋን ገጽታ በከፍተኛ ደረጃ መቀየራቸውን ገልጸዋል። የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶችም አዲስ የሥራ ባህል ተፈጥሮባቸው በአጭር ጊዜና በጥራት ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ መደረጉንም አንስተዋል። በከተማዋ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ እና ፍትሐዊ አገልግሎት በመስጠት ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ የተቻለ ሲሆን ከ75 ሺህ በላይ ነዋሪዎች አገልግሎቱን እንዲያገኙ መደረጉን ጠቁመዋል።   የከተማ አስተዳደሩ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞላ ሁሴን በበኩላቸው፤ በከተማዋ ከጊዜ ወደ ጊዜ አስተማማኝ ሰላም እየሰፈነ መምጣቱን ገልጸዋል። የተገኘው ሰላም ለማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማቶች መሳካት ቁልፍ መሠረት በመሆኑ ቀጣይነት እንዲኖረው ሁለንተናዊ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የታዩ ክፍተቶችን በማረም በአዲሱ በጀት ዓመት የላቀ ውጤት ለማስመዝገብና ከተማዋን ይበልጥ ለማልማት ሁሉም በቅንጅት መስራት እንዳለበት አሳስበዋል።
በዞኑ በምርት ዘመኑ 28 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ የሚያስችሉ ተግባራት እየተካሄዱ ነው
Sep 14, 2026 107
ባህር ዳር፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ጎንደር ዞን በመኸር ወቅት ከለማው 641 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ከ28 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ የሚያስችል የተባይ አሰሳና የአረም መከላከል ስራ እየተከናወነ ይገኛል።   የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ የሺጥላ ፈቃዴ እንደገለጹት፤ በዞኑ በኩታ ገጠም አሰራር እየለሙ ያሉትን እንደ ሩዝ፣ ጤፍ፣ ስንዴ እና ገብስ ያሉ ሰብሎችን ከአረምና ተባይ ነፃ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ ነው። ሙሉ የግብርና ፓኬጅ፣ የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችና የአፈር ለምነት ማሻሻያዎች በጥቅም ላይ በመዋላቸው ሰብሉ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝና የታቀደው ምርት እንደሚገኝ ተናግረዋል።   የዞኑ አርሶ አደሮች በበኩላቸው፤ በባለሙያዎች ምክረ-ሃሳብ ታግዘው ማሳቸውን በየዕለቱ በመቃኘትና በማረም ላይ እንደሚገኙ ገልጸው፣ የኩታ ገጠም አሰራርና ዘመናዊ ግብዓቶችን መጠቀም ከቤተሰብ ፍጆታ የተረፈ ምርት ለገበያ ለማቅረብ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል።  
በዞኑ በማር ምርት የተገኘው ውጤት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Sep 14, 2026 176
ዲላ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በማር ምርት የተገኘውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያስችሉ ተግባራትን መጀመራቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በዞኑ እየተከናወነ ያለውን የጥምር የግብርና ስርዓት ለንብ ማነብ ስራ አመቺ ሁኔታ በመፍጠሩ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን ተችሏል። በጥምር ግብርናው ቡና፣ ፍራፍሬ፣ ሃገር በቀል ዛፎችንና የተለያዩ እጽዋቶችን ከማልማት ባለፈ ለንብ ማነብ ስራዎችም የተመቸ ምህዳር ፈጥሯል ነው የሚሉት። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ በዞኑ ከተከናወነው የንብ ሃብት ልማት ስራ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱ ተገልጿል። በዚሁ ወቅት በተለይ ተራሮችን የማር ምርት ማዕከል ለማድረግ በተደረገው ጥረት በዲላ ዙሪያ፣ ወናጎ፣ ይርጋጨፌና ኮቾሬ ወረዳዎች በተመረጡ ቦታዎች ከአንድ ሺህ በላይ ዘመናዊ ቀፎ ማስቀመጥ መቻሉን ተናግረዋል። በንብ ማነብ ስራ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች በተጨማሪ በማህበር የተደራጁ ወጣችን ወደ ስራው እንዲገቡ ማድረግ በመቻሉ በዘርፉ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን እንደተቻለም ነው የገለጹት። በአዲሱ በጀት ዓመትም የአካባቢውን የደንና የእጽዋት ሽፋን በመንከባከብ ንብ በማነብ ከማር ምርት የሚገኝ ገቢን ከፍ ለማድረግ ወደ ስራ መገባቱን ነው ያመለከቱት። በወረዳው በራኮ ቀበሌ በግኖ ተራራ ላይ ከ200 በላይ ዘመናዊ ቀፎዎች በማስቀመጥ የንብ ማነብ ስራ እየተካሄደ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የኮቾሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ዳዊቶ ጀቦ (ዶ/ር) ናቸው። ይህም የማር ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፍ የተፈጥሮ ጸጋዎችን በመንከባከብና በማልማት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ጥራት ያለው የተፈጥሮ ማር በማምረት ለአካባቢው አርሶ አደሮች፣ ወጣቶች እና ሴቶች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ መፍጠር እንደተቻለም ነው ያነሱት። በማር ምርት ስራ ላይ የተሰማሩት አርሶ አደር ብዙነሽ ሐልቹ፤ ከ70 በላይ በሆኑ ባህላዊና ዘመናዊ ቀፎዎቻቸው በአመት ሁለት ጊዜ የማር ምርት እንደሚያገኙ ነው የተናገሩት። የማር ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆኑንም ነው የተናገሩት። ከዘመናዊ ቀፎ የሚገኝ የማር ምርት የተሻለ ጥራትና ብዛት ያለው መሆኑን ያነሳው ደግሞ በማር ምርት ስራ ላይ የተሰማራው ወጣት ማርቆስ ጌታሁን ነው። በወረዳው ያለው የተፈጥሮ ሃብት ለንብ ማነብ ስራ ምቹ በመሆኑም ጥራት ያለው ማር በማምረት በስፋት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆኑን ነው የተናገረው።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኃይል አቅርቦቱን በእጥፍ በማሳደግ የቀጣናውን የኢኮኖሚና የኃይል ትስስር እያጠናከረ ነው
Sep 14, 2026 591
አዲስ አበባ፤መስከረም4 /2019 (ኢዜአ):-ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሀገሪቱን የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ከእጥፍ በላይ ከማሳደግ ባለፈ የቀጣናውን የኃይል ትስስር እያጠናከረ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ አስታወቁ። ዋና ሥራ አስፈጻሚው ለኢዜአ እንዳሉት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያውያን ጽናት፣ አንድነትና ቁርጠኝነት በተግባር የተገለጠበት «ዳግማዊ ዓድዋ» መሆኑን ተናግረዋል። የግድቡ ግንባታ ኢትዮጵያ በራሷ አቅም የላቀ ስኬት ማስመዝገብ እንደምትችል ለዓለም ያስመሰከረችበት፤ ብሎም አዲስ የታሪክ ምዕራፍ የከፈተ ታላቅ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። ግድቡ ተመርቆ ወደ ሙሉ ሥራ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ የሀገሪቱን የኃይል ማመንጨት አቅም በእጥፍ ከመጨመሩም በላይ፣ ኢትዮጵያ ከዘርፉ የምታገኘውን የውጭ ምንዛሬ ገቢ በእጅጉ ማሳደጉን ገልጸዋል። ተቋሙ በ2018 በጀት ዓመት በሀገር ውስጥ ካገኘው ከፍተኛ ገቢ በተጨማሪ ከግማሽ ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማግኘቱን ጠቁመው፤ ለዚህ ታሪካዊ ስኬት የታላቁ ህዳሴ ግድብ ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን አስረድተዋል።   በዚህም የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ከዕዳ ተላቆ ወደ ትርፋማነት እንዲሸጋገር ማስቻሉን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በተመጣጣኝ ዋጋ ለጎረቤት ሀገራት ኃይል እያቀረበች መሆኑን የጠቆሙት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ የግድቡ ወደ ሥራ መግባት ለቀጣናዊ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ትስስር ማደግ አይነተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ለኬንያ፣ ለጅቡቲ፣ ለሱዳን እና በከፊል ለታንዛኒያ የኤሌክትሪክ ኃይል በማቅረብ ላይ መሆኗን የጠቆሙት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ ወደ እነዚህ ሀገራት ከሚላከው አጠቃላይ ኃይል ውስጥ 52 በመቶ የሚሆነው ድርሻ ከህዳሴው ግድብ የሚመነጭ መሆኑን አመላክተዋል።   የኃይል አቅርቦቱን በእጥፍ በማሳደግ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ብቻ ሳይሆን ለጎረቤት ሀገራትም ከፍተኛ የኤሌክትሪክ አቅርቦት ጥቅም እየሰጠ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።  
በጅማ ዞን የተቀናጀ የቡና ልማትና የጥራት እንክብካቤ ስራን በስፋት በመተግበር አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ሆነዋል
Sep 14, 2026 329
ጅማ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን የተቀናጀ የቡና ልማትና የጥራት እንክብካቤ ስራን በስፋት በመተግበር ከምርቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ገለጹ። በጅማ ዞን ቀደም ሲል የሚሰበሰበው የቡና ምርት በጥራትና በድህረ-ምርት አያያዝ ጉድለት ምክንያት አርሶ አደሩን በሚፈለገው ልክ ተጠቃሚ ሳያደርግ ቆይቷል። ይህንን ችግር ለመቅረፍ በዞኑ አመራርና ባለሙያዎች አስተባባሪነት ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተቀናጀ የቡና ልማትና የጥራት ማሻሻያ ተዘጋጅቶ ወደ ተግባር ተገብቷል። በልማቱ ተሳታፊና ተጠቃሚ የሆኑት አርሶ አደሮች እንዳሉት፣ ጥራቱን የጠበቀ የቡና ምርት በቀጥታ ለገበያ የሚያቀርቡበት አሰራር በመዘርጋቱ፣ ከቀጥታ የገበያ ትስስሩ የሚገኘው ገቢ ተጠቃሚነታቸውንና የኑሮ ደረጃቸውን እንዲሻሻል አድርጎታል።   በዞኑ የጎማ ወረዳ አርሶ አደር ሙስጠፋ አባ ቀኖ፣ በአሁኑ ወቅት መንግስት ባመቻቸው የቀጥታ የገበያ እድል የደላሎች ጣልቃ ገብነት በመቅረቱ፣ ቡናቸውን በጥራትና በስፋት አዘጋጅተው ለገበያ ማቅረብ መቻላቸውን ተናግረዋል። ቡናን በቀጥታ ለውጭ ገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን ጠቅሰው፣በጥራት እና በቴክኖሎጂ በተደገፈው አሰራር ከአንድ ሄክታር እስከ 10 ኩንታል ምርት በማግኘት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። አሰራሩ ገቢያቸውን ከማሳደጉም በላይ ለሀገሪቱ የውጭ ምንዛሬ ግኝት የድርሻቸውን እንዲያበረክቱ ማስቻሉንም አብራርተዋል።   ሌላኛው የዞኑ አርሶ አደር ዛኪር አባፊጣ በበኩላቸው፣ ባለፉት ዓመታት ከተለምዷዊ አሰራር በመላቀቅ ቡናን በኩታገጠም በጥራት ማምረት መጀመራቸውን ገልጸዋል። በኩታገጠም የሚከናወነው የልማት ስራ የሙያና የቴክኖሎጂ ድጋፍን በጥንቃቄ ለመተግበር በመርዳቱ፣ የምርት ጥራትንና ምርታማነትን በከፍተኛ ደረጃ እንዳሳደገው ገልጸዋል። በቡና ልማት ትርፋማ መሆናቸውን የገለጹት አርሶ አደር ዛኪር፣ ከዘርፉ ባገኙት ገቢ በቅርቡ ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ጠቅሰዋል። ይህም በጥራትና በኩታገጠም የተመራ የግብርና ልማት አርሶ አደሩን ወደ ባለሃብትነት ለማሸጋገር ያለውን አቅም ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።   ወጣት አርሶ አደር ቡሊ አባመጫ በበኩሉ፣ ቡናን በጥራት በማምረት ለገበያ እያቀረበ መሆኑን ገልጿል። በቅርቡ በተጠናቀቀው የቡና ምርት ዘመን ከ20 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ ጥራት ያለው ቡና ለገበያ ማቅረቡንና ከዘርፉ የሚገኘው ጥቅም የወጣቶችን የኢኮኖሚ ተሳትፎ የሚያጎለብት መሆኑን አብራርቷል። አርሶ አደር ኤሊያስ አባሰዲም፣ ከዚህ በፊት ከሚያመርቷቸው የቡና ተክሎች በተጨማሪ በየወቅቱ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ምርጥ ዘር የቡና ችግኞች ፍሬ አፍርተው ምርት መስጠት መጀመራቸውን ተናግረዋል።   አሰራሩ የቀደመውን የምርት አቅም በማጎልበት ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ገልጸው፤ ይህም የምርት መጠናቸውንና አምራችነታቸውን በከፍተኛ ሁኔታ ከፍ እንዳደረገላቸው ገልጸዋል። አርሶ አደሮቹ እንደገለጹትም፣ መንግስት ለቡና ምርት ጥራትና መስፋፋት በሰጠው ትኩረት አማካኝነት አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍና ክትትል መደረጉ ለቡና ልማቱ መስፋፋትና ለውጤታማነቱ ዋና ምክንያት ነው።   የጅማ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም እንደገለጹት፣ በዞኑ ባለፉት ሰባት ዓመታት የቡና ምርት ሽፋን ከ330 ሺህ ሄክታር ወደ 700 ሺህ ሄክታር አድጓል። የቡና ልማት ሽፋኑ በከፍተኛ ደረጃ ማደጉ ምርታማነትንና የጥራት ደረጃን ከመጨመሩ ባሻገር የአርሶ አደሩን የገቢ አቅም ያጎለበተ መሆኑንም አብራርተዋል። አርሶ አደሩ ምርቱን በቴክኖሎጂና በኩታገጠም በጥራት በማልማት ያለምንም ጣልቃ ገብነት በቀጥታ ለገበያ የሚያቀርብበት ምቹ ሁኔታም ተፈጥሯል ብለዋል። በዚህም በተጠናቀቀው ዓመት ከተሰበሰበው 341 ሺህ ቶን ቡና ውስጥ 94 ሺህ ቶኑ ለዓለም አቀፍ ገበያ የቀረበ ሲሆን፣ ይህም ለሀገር የውጭ ምንዛሬ ከማስገኘት ባሻገር አርሶ አደሩን የኢንቨስትመንት ባለቤት እስከ መሆን ያደረሰ አቅም ፈጥሯል ብለዋል።    
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አባልና አጋር ሀገራትን ባሳተፈው የብሪክስ ፕላስ የምክክር መድረክ ላይ፤ጠንካራ የአፍሪካ ውክልና እንዲኖር ጥሪ አቅርበዋል
Sep 13, 2026 607
አዲስ አበባ፤መስከረም 3 /2019 (ኢዜአ):-አባልና አጋር ሀገራትን ባሳተፈው የብሪክስ ፕላስ የምክክር መድረክ ላይ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጠንካራ የአፍሪካ ውክልና እንዲኖር፣ የፋይናንስ እና የገበያ ተደራሽነት ይበልጥ እንዲሰፋ እንዲሁም ንግድ፣ ኢንቨስትመንት እና ትስስርን ለማሳደግ ተግባራዊ እርምጃዎች እንዲወሰዱ ጥሪ አቅርበዋል። ‎‎በዚህ አውድም፣ የኒው ዴቨሎፕመንት ባንክ አድማሱን በመላው አፍሪካ እንዲያስፋፋ የባንኩን ቢሮ በአዲስ አበባ ለማስተናገድ ኢትዮጵያ በሙሉ አቅም ዝግጁ መሆኗን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። ‎‎በተጨማሪም በአዲስ አበባ የሚካሄደው ኮፕ 32 በብሪክስ ሙሉ ድጋፍ ለአየር ንብረት ጥበቃ ሥራዎች እና ለዘላቂ ልማት መፋጠን ሁሉንም ድምፆች የሚያሰባስብ ሁሉን አቀፍ መድረክ ሆኖ ማገልገል እንደሚችል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል። ‎‎#PMOEthiopia
የኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ድምጾች በብሪክስ መድረክ ተስተጋብተዋል-የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
Sep 13, 2026 392
አዲስ አበባ፣መስከረም 3/ 2019 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ድምጾች በብሪክስ መድረክ መስተጋባታቸውን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለፀ፡፡ አገልግሎቱ በዛሬው ዕለት ባወጣው መግለጫ፤ የኢትዮጵያ በሳል ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ብዙ ሀገራት የሚመኙትን የብሪክስ አባል የመሆን መሻት እንድታሳካና ተጠቃሚ እንድትሆን አስችሏታል ብሏል። የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡ የኢትዮጵያ ስትራቴጂያዊ ድምጾች በብሪክስ መድረክ ተስተጋብተዋል! ብሪክስ ወደ ሰፊ ጥምረት አድጓል፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ አሁን 11 ሙሉ አባላት ያሉት ሲሆን በሩሲያ ካዛን ጉባኤ ይፋ የተደረጉ 10 አጋር አገራትንም በልዩ የአጋርነት ማዕቀፍ በማካተት ተጽእኖውን አጠናክሯል። የብሪክስ ጥምረት የዓለምን ሕዝብ ቁጥር ግማሽ ያህል፣ የዓለም አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርትን (GDP) 40 በመቶ ገደማ፣ እና የዓለምን ንግድ ሩብ ያህል ይወክላል። መጠኑ እጅግ ግዙፍ ነው። ብሪክስ ከእንግዲህ ተራ ጥምረት ብቻ አይደለም፤ በዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ሥርዓት ውስጥ ዋነኛ ኃይል እየሆነ ነው።   የብሪክስ አባል ሀገራት በአለምአቀፍ ደረጃ የተጽዕኖ አድማሳቸው የሰፋ፣ የዓለም አቀፍ የሀብት፣ የቴክኖሎጂ እና የሰፊ ገበያ ማዕከል መዳረሻ ናቸው። የኢትዮጵያ በሳል ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ብዙ ሀገራት የሚመኙትን የዚህ ጥምረት አባል የመሆን መሻት እንድታሳካና ተጠቃሚ እንድትሆን አድርጓታል። በዚህ ሂደት ኢትዮጵያ የራሷን ጥቅም ከማስጠበቅ ባለፈ ለአፍሪካ ድምፅ በመሆን የአህጉሪቱን ጥያቄዎች እና የጋራ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሥራዎችን በቁርጠኝነት እየሠራች ትገኛለች። ከቀሪ የቤት ሥራዎች አንዱ ይህን ታሪካዊ ዕድል በመጠቀም የጥምረቱን ግዙፍ አቅሞች በማስተሳሰር የላቀ እሴት መፍጠር እና ይህ እሴት ሀብቱ በቀጥታ በሚገኝበት አካባቢ እንዲመረት ማድረግ ነው። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ በማዕድን ልማት፣ በታዳሽ ኃይል እና በማደግ ላይ ባለው የኢንዱስትሪ መሠረቷ ላይ እነዚህን ስትራቴጂካዊ አጋርነቶች እውን ለማድረግ ሙሉ ዝግጁነት አላት።   በማዕድን ዘርፍ ኢትዮጵያ ያሏትን እንደ ሊቲየም፣ ታንታለም እና ፖታሽ ያሉ ለዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ እና የኢነርጂ ሽግግር ወሳኝ የሆኑ ሀብቶችን በሀገር ውስጥ በማቀነባበር የኢንዱስትሪ እሴት ሰንሰለቱን ለመቀላቀል ሰፊ ሥራዎችን እየሠራች ይገኛል። ይህ እንቅስቃሴ የሀብት ባለቤት የሆኑ ሀገራት ከጥሬ ዕቃ ላኪነት ወጥተው የተጠናቀቁ ምርቶች አምራች እንዲሆኑ የሚያስችል የጋራ የኢኮኖሚ ምዕራፍ ይፈጥራል። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ያላትን ግዙፍ የታዳሽ ኃይል አቅም በመጠቀም አረንጓዴ እና ንጹህ የኢነርጂ አቅርቦትን ለሀገራት ማዳረስ ትችላለች። የውኃ፣ የጂኦተርማል እና የሶላር ኃይል ሀብቶችን በማልማት ለቀጣናው እና ለአጋሮች አስተማማኝ የኃይል ማዕከል ለመሆን የሚያስችል ጠንካራ መሠረት ይጥላል። ኢኮኖሚያዊ ትስስሩ ከሀብት ማውጣትና ማቀነባበር ባሻገር በቴክኖሎጂ ሽግግር እና በተቋማዊ ጽናት ላይ የተመሠረተ መሆን ይኖርበታል። የአሠራር ሥርዓቶቻችንን በማጠናከር እና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (AI)ን ጨምሮ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች የአፍሪካን ልማታዊ እና ማህበራዊ ፍላጎቶች በትክክል እንዲያገለግሉ የጋራ ጥረቶችን ማቀናጀት ያስፈልጋል። ለዚህም ኢትዮጵያ ቁርጠኛ ናት። ለዘላቂ ዕድገት መረጋገጥ የፋይናንስ ሥርዓቶች ፍትሃዊ መሆን አለባቸው፤ በዚህ ረገድ በማደግ ላይ ያሉ ሀገራትን የዕዳ ጫና የሚያቃልል አስተማማኝ እና ፍትሃዊ የዕዳ እፎይታ ሒደት ማሳደግ ወሳኝ ነው። የብሪክስ መድረክ የደቡብ-ደቡብ ትብብርን በመጠቀም ፍትሃዊ የዓለም አቀፍ የፋይናንስ ሥርዓት እንዲዘረጋ ጠንካራ ድምፅ ማሰማት የሚችልበት አቅም አለው። ከኢኮኖሚ ሽግግር ጎን ለጎን የአየር ንብረት ጥበቃ ሥራዎችን ከምግብ ዋስትና እና ከዘላቂ ልማት ጋር ማስተሳሰር ይገባል። እንደ ኢትዮጵያ «የአረንጓዴ አሻራ» ተነሳሽነት ያሉ አሠራሮች ለአየር ንብረት ጽናት የሚሰጡትን አስተዋጽኦ በማስፋት የብሪክስ መድረክ የጋራ ትብብርን ወደ ተጨባጭ እሴት፣ ጽናት እና ዘላቂ የጋራ ዕድገት ለመለወጥ የሚያስችል ታሪካዊ ዕድል ይፈጥራል። ኢትዮጵያም ይህን ዕድል የአፍሪካ ድምጽ በመሆን ጭምር መጠቀም ጀምራለች ።
የአውሮፓ ህብረትና አባል ሀገራት ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ሪፎርምና አካታች ልማት የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው ይቀጥላሉ
Sep 13, 2026 349
አዲስ አበባ፤መስከረም 3 /2019 (ኢዜአ):-የአውሮፓ ህብረትና አባል ሀገራት ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ሪፎርምና አካታች ልማት የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በኢትዮጵያ የአውሮፓ ህብረት አምባሳደር ሶፊ ፍሮም-ኤምስበርገር ገለጹ። የአውሮፓ ህብረት ኢትዮጵያ ለጀመረችው አጠቃላይ የኢኮኖሚ ማሻሻያና ሌሎች የልማት ሥራዎች ድጋፉን አጠናክሮ ይቀጥላልም ብለዋል። አምባሳደር ሶፊ ፍሮም-ኤምስበርገር ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተግባራዊ ማድረግ ከጀመረች ወዲህ አስደናቂ ውጤት አስመዝግባለች። መንግሥት የተሟላ የኢኮኖሚ ማሻሻያ እርምጃዎችን ተግባራዊ በማድረግ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን ገልጸዋል። የኢኮኖሚ ማሻሻያው ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ጠቁመው፣ ትግበራውን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ አሳስበዋል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና በአፍሪካ ሀገራት መካከል ያለውን ንግድ በማስፋት አህጉራዊ አቅማቸውን እንደሚያሳድግ ገልጸዋል። ጠንካራ የኢኮኖሚ ትስስር መፍጠር ለንግድ፣ ለኢንቨስትመንት እና ለዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። የአውሮፓ ህብረት እና አባል ሀገራቱ ለኢትዮጵያ የልማት ግቦች ስኬት ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸው፤ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን፣ በኃይል፣ በጤና እና በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ዘርፎች የላቀ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ አረጋግጠዋል። አዲስ አበባ የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ፣ የአህጉሪቱ የዲፕሎማሲ፣ የትብብር እና የፖሊሲ ዋና ማዕከል መሆኗን ጠቅሰው፤ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታዋንም አንስተዋል። የአውሮፓ ህብረት እና ኢትዮጵያ በጠንካራ እና አስተማማኝ አጋርነት ላይ የተመሰረተ መልካም ግንኙነት እንዳላቸው ገልጸዋል። ለዚህም ህብረቱና አባል ሀገራቱ ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረጋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያና እስራኤል ጠንካራ የዲፕሎማሲ ግንኙነት የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብርን ለማጎልበት ምቹ ምኅዳር ፈጥሯል - አምባሳደር አብርሃም ንጉሤ (ዶ/ር) 
Sep 13, 2026 277
አዲስ አበባ፤ መስከረም 3 /2019 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያና እስራኤል ጠንካራ የዲፕሎማሲ ግንኙነት የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብርን ለማጎልበት ምቹ ምኅዳር መፍጠሩን በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ገለጹ። አምባሳደር አብርሃም ንጉሤ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያና እስራኤል ግንኙነት ታሪክን ከዘመናዊ የዲፕሎማሲ ትብብር ጋር በማሰናሰል በሁሉም መስክ እየጎለበተ የመጣ ነው። በአሁኑ ወቅትም በመንግሥት ለመንግሥት፣ በግሉ ዘርፍ ንግድና ኢንቨስትመንት እንዲሁም መንግሥታዊ ባልሆኑ የልማት ድርጅቶች አጋርነት በሁሉም ዘርፍ ውጤታማ ትብብር መፈጠሩን ገልጸዋል። ይህም የሀገራቱን የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት በማጎልበት በኢኮኖሚ፣ ማኅበራዊና ፖለቲካዊ የትብብር መስኮችን በማስፋት የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያጎለብት አስቻይ ምህዳር መፍጠሩን ተናግረዋል። የኢትዮጵያና እስራኤል ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናት የእርስ በእርስ ይፋዊ የሥራ ጉብኝትም የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያጎለብት መግባባትን በመፍጠር ጉልህ ሚና እየተወጣ መሆኑን አንስተዋል። የእስራኤል በበጎ አድራጎት ድርጅቶች ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን አመልክተው፤ ከነዚህ መካከል በጤናው ዘርፍ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠቃሽ መሆናቸውን አመልክተዋል። የእውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግር፣ የልምድ ልውውጥ በማድረግና በተለያዩ መስኮች ላይ የሙያተኞችን አቅም በሥልጠና በማብቃት የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት ማጠናከር ተችሏልም ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ከ100 በላይ የሚሆኑ የእስራኤል ኩባንያዎች በልዩ ልዩ የኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት አማራጮች ተሰማርተው እንደሚገኙ አስታውቀዋል። ኢትዮጵያ ለእስራኤል የምሥራቅ አፍሪካ ቁርጠኛ አጋር እንደሆነች ሁሉ እስራኤልም ለኢትዮጵያ የመካከለኛው ምስራቅ ቁርጠኛ ወዳጅ መሆኗን አስረድተዋል። የሀገራቱን የጋራ ተጠቃሚነት ለማላቅ በሚደረገው ጥረትም የኢትዮጵያ አየር መንገድና የእስራኤል የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ቁልፍ ሚና እየተወጡ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ከአዲስ አበባ እስከ ቴል አቪቭ የአራት ሰዓታት የቀጥታ በረራ ብቻ የሚወስድ መሆኑም የእርስ በእርስ የንግድና አገልግሎት ልውውጡን በአጭር ሰዓታት ለማሳለጥ መልካም አጋጣሚ መፍጠሩን አብራርተዋል። ይህም እስራኤል የኢትዮጵያ የግብርና ምርቶችን ኢትዮጵያ ደግሞ የፈጠራና የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በወጪና ገቢ የንግድ ልውውጥ እንዲሳለጥ በማድረግ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑን አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ መመስረት፣ አዲስ አበባ የአፍሪካና የዓለም አቀፍ የፖለቲካል ዲፕሎማሲ ማዕከል ሀገር መሆኗም እስራኤል ለኢንቨስትመንት የምትመርጣት ሀገር እንድትሆን አስችሏታል ብለዋል። የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያና የዲጂታል ልማት የእስራኤል ባለሀብቶች በተለያዩ የንግድና ኢንቨስትመንት መስኮች መዋለ ነዋያቸውን የሚያፈሱበትን ምቹ መደላድል እንደፈጠረ ገልጸዋል። ይህም እስራኤል የኢትዮጵያ የግብርና ምርቶችን፣ ኢትዮጵያ ደግሞ የፈጠራና የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በወጪና ገቢ የንግድ ልውውጥ እንዲሳለጥ በማድረግ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑን አብራርተዋል።  
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር  ኑሯችንን አሻሽሏል- በድሬደዋ በዘርፉ የተሰማሩ
Sep 13, 2026 109
ድሬዳዋ፤ መስከረም 3/2019 (ኢዜአ)፡- በድሬደዋ ከተማ አስተዳደር የሌማት ትሩፋት መርሃግብር ኑሯቸውን ማሻሻሉን ተጠቃሚዎች ገለጹ። በመርሃግብሩ የተገኙ ውጤቶችን በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የገለጸው ደግሞ የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና ፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ነው። የሌማት ትሩፋት መርሃግብር ተጠቃሚ የሆኑት አቶ በቀለ ኑረሳ ለኢዜአ እንደገለፁት ፤ ቢሮው የተሻለ የወተት ምርት የሚሰጡ ላሞችን ስላቀረበላቸው ወተት ወደ ገበያ በማቅረብ የተሻለ ገቢ እያገኙ ነው።   ለአካባቢው ማህበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ ጥራቱን የጠበቀ ወተት በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው፤ ከወተት ምርት ያገኙትን ሀብት ተጨማሪ የወተት ላሞችን ለመግዛት እየተጠቀሙበት መሆኑን አቶ በቀለ ተናግረዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተካተቱ ወዲህ ኑሯቸውን እየቀየሩ መምጣታቻውን ገልጸዋል። ከንብ ማነብ ስራ ባገኙት ጥቅም ስራውን ይበልጥ እንዲገፉበት እንዳደረጋቸው የገለፁት ደግሞ ሌላው የሌማት ትሩፋት ኢንሼቲቭ ተጠቃሚ አቶ አብዱልቃድር ሁሴን ናቸው።   ባለፈው ግንቦትና ሰኔ ወራት ብቻ ከ400 ኪሎ ግራም በላይ የማር ምርት ማግኘታቸውን አስታውቀዋል። ስራው ጥንቃቄ እና እንክብካቤ እንደሚፈልግ የገለፁት አቶ አብዱልቃድር፤ ከግብርና ባለሙያዎች ጋር በትስስር መስራታቸው ይበልጥ ለማስፋፋት እንዳገዛቸው ተናግረዋል ። ስራው ወደ ሌሎች አርሶአደሮች መንደር እንዲስፋፋ ከግብርና ቢሮ ጋር ተቀናጅተው እየተንቀሳቀሱ መሆኑንም ጠቅሰዋል።   የግብርና ቢሮ ምርጥ የዕንቁላል ዶሮዎች እና የእርባታ ስፍራ በማመቻቸቱ ወደ ስራ በመግባት ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እንዳስቻላቸው የተናገሩት ደግሞ በገንደሳር ገጠር ቀበሌ በእንቁላል ማምረት ስራ የተሰማሩ ወይዘሮ አያን መሐመድ ናቸው። የማህበሩ አባላት ዶሮዎቹን በአግባቡ በመንከባከብ የሚያመርቱትን እንቁላል በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ እያቀረቡ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የድሬደዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ሚስራ አብደላ የሌማት ትሩፋት መርሃግብር ገጠሩን ህብረተሰብ የእንሰሳት ሃብቱን በአግባቡ ተጠቅሞ ኑሮውንና ህይወቱን እንዲለውጥ እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል ።   በዚህም በርካታ የገጠርና የከተማ ቤተሰቦች ተገቢውን ስልጠና፣ ድጋፍ እና ክትትል በማድረግ የማር፣ የዶሮ ፣ የእንቁላል እና የወተት ምርቶች በስፋት ማምረት መቻላቸውን ገልፀዋል፡፡    
ሀገራት በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ ፍትሃዊ ውክልና ሊኖራቸው ይገባል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 12, 2026 289
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ):- በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ ፍትሃዊና ተደማጭነታቸውን ያረጋገጠ ውክልና ሊኖራቸው እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። 18ኛው የብሪክስ ጉባኤ ዛሬ በህንድ ኒው ዴልሂ መካሄድ ጀምሯል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር የማዕድን ሀብት ለኢነርጂ ሽግግር፣ ለላቀ ማኑፋክቸሪንግ እና ለዲጂታል ኢኮኖሚ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። አፍሪካ የበርካታ ማዕድናት ሀብት ባለቤት መሆኗን ጠቅሰው፤ የብሪክስ አባል ሀገራት ደግሞ የካፒታል፣ የቴክኖሎጂ እና የገበያ አማራጭ እንዳላቸው አንስተዋል። እነዚህን ሀብቶች አቀናጅቶ ለመጠቀምና በጥሬ ሃብቱ ላይ እሴት ለመጨመር የብሪክስ ጥምረት ትልቅ እድልን የሚፈጥር መሆኑን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በማዕድናት፣ በታዳሽ ኢነርጂ እና እያደገ ያለውን የኢንዱስትሪ አቅሟን መሰረት ባደረገ መልኩ አጋርነቶችን ለመፍጠር ዝግጁ መሆኗን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ ለአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ትስስር ያላት አበርክቶ ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አፍሪካን ከዓለም ጋር እያገናኘ እንደሚገኝ በማሳያነት ጠቅሰዋል። ለጎረቤት ሀገራት የምታቀርበው የኤሌክትሪክ ኃይል ለሀገራቱ ኢኮኖሚ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ አዲስ አበባ የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ መሆኗንም አንስተዋል። ኢትዮጵያ ብሪክስ እና የአፍሪካ ህብረት ያላቸው ትብብር ከአጀንዳ 2063 ጋር የተጣጣመ እንዲሆን ድጋፏን እንደምትሰጥም አመልክተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ስርዓት ጋር በተያያዘ ባነሱት ሀሳብ የኢኮኖሚ ሪፎርም ማድረጓን እና የውጭ ዕዳዋን ለማሸጋሸግ እየሰራች መሆኗን ገልጸዋል። በፈተና ውስጥ ለሚገኙ ኢኮኖሚዎች ጊዜ ውድ ሀብት መሆኑን ጠቅሰው፤ የዕዳ አከፋፈል ሂደት ፈጣን፣ ግልጽ እና ተገማች መሆን እንዳለበት አሳስበዋል። ሀገራት በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ ያላቸው ውክልና ፍትሃዊ መሆን እንዳለበት ጠቅሰው፤ ውክልናው ተጨባጭ ውጤት ማምጣት እንዳለበትም አስገንዝበዋል።
‎‎በብሪክስ አባል ሀገራት ዘንድ ሀብት፣ ቴክኖሎጂ እና ሰፊ ገበያ አለን-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 12, 2026 157
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ)፦‎‎በብሪክስ አባል ሀገራት ዘንድ ሀብት፣ ቴክኖሎጂ እና ሰፊ ገበያ አለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ጽናትን፣ ፈጠራን፣ ትብብርን እና ዘላቂነትን መገንባት በሚል መሪ ቃል በሕንድ ኒው ዴልሂ እየተካሄደ በሚገኘው 18ኛው የብሪክስ ጉባኤ ላይ አካል በመሆናችን ኩራት ይሰማናል ብለዋል።   ‎‎በብሪክስ አባል ሀገራት ዘንድ ሀብት፣ ቴክኖሎጂ እና ሰፊ ገበያ አለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁን ያለው መልካም ዕድል እነዚህን አቅሞች በማስተሳሰር የላቀ እሴት መፍጠር እና ይህ እሴት ደግሞ ሀብቱ በሚገኝበት ቦታ መመረት እንዲችል ማድረግ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በማዕድን ልማት፣ በታዳሽ ኃይል እና እያደገ በሚገኘው የኢንዱስትሪ መሠረቷ ላይ እነዚህን አጋርነቶች ለመገንባት ዝግጁ ናትም ብለዋል።   ‎‎በተጨማሪም በአሠራር ሥርዓቶቻችን ውስጥ ጽናትን መገንባት፣ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የአህጉራችንን ፍላጎት እንዲያገለግል ማድረግ፣ አስተማማኝ የዕዳ እፎይታ ሒደትን ማሳደግ እንዲሁም የአየር ንብረት ጥበቃ ሥራዎችን ከኢኮኖሚ ሽግግር ጋር ማስተሳሰር ይኖርብናል ሲሉም ገልጸዋል። ‎‎የብሪክስ መድረክ የጋራ ትብብርን ወደ የጋራ እሴት፣ ጽናት እና ዘላቂ ዕድገት የመለወጥ ሰፊ አቅምና ቁርጠኝነት እንዳለውም ነው ያመላከቱት።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም