ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የከተሞች ትንሣኤ፡- የልማት አሻራ፣ የዕድገት እጥፋትና የነገው ብሩህ ተስፋ
May 22, 2026 68
የከተማ ልማት ዕሳቤና ፖሊሲ የከተማውን ኅብረተሰብ መሠረታዊ ጥያቄዎች የሚመልስ ሥርዓት መገንባትን ቀዳሚ ያደረገ ነው። ከተሞችን ተስማሚ የመኖሪያ ሥፍራ ብቻ ሳይሆን አካታች፣ ስማርት እና ለኑሮ ምቹ የሆኑ የብልፅግና ማዕከላት የማድረግ ራዕይ ተይዟል። ዋነኛ ግቡም ከተሞችን የሁሉም ዜጎች የጋራ መኖሪያ ማድረግ፣ ፍትሓዊ የቤት አቅርቦትን ማረጋገጥ እና የዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ማዕከላት ማድረግ ነው። መንግሥት “መደመርን” እንደ መንገድ በመውሰድ የከተሞችን ተግዳሮት ወደ ልማት ዕድሎች የመቀየር ስትራቴጂን ተግባራዊ አድርጓል። በዚህም የገጠር-ከተማ ትሥሥርን በማጠናከርና የተሰባሰበ አሰፋፈር ያላቸውን ከተሞች በመፍጠር ለነገው ትውልድ የምትመች አገር የመገንባት ታላቅ ሥራ ተጀምሯል። የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና የማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች ለዜጎች በተሻለ ቅልጥፍና እንዲቀርቡ የተደረገ ቢሆንም፣ ከተሞችን በተቀናጀ የረጅም ዘመን ፕላን የመምራት ውስንነት፣ የመረጃ አያያዝ ችግሮች እና ገቢን በሥርዓት አለመሰብሰብ አሁንም የሚታዩ ክፍተቶች ናቸው ። እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍም ተቋማዊ ሪፎርሞች በቁርጠኝነት እየተከናወኑ ይገኛሉ። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በከተማ ልማት ዘርፍ ሞዴል ሥራዎች በፍጥነትና በጥራት ተከናውነዋል። ለአብነትም መዲናችን አዲስ አበባ በወንዝ ዳርቻ እና በኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች አማካይነት የአፍሪካ የከተማ ልማት ሞዴል እንድትሆን ተደርጋለች። የጫካ ኢኮ-ስማርት ሲቲ ፕሮጀክት አረንጓዴ ኢኮኖሚንና ዘመናዊ መሠረተ ልማትን ያዋሐደ ትልቅ ስኬት ሲሆን፣ የጣና ዳርቻ፣ የጅማ የሥነ-ምኀዳርና የሐረር የኮሪደር ልማት ሥራዎች የመንግሥትን ሁለንተናዊ የለውጥ ዐቅም አሳይተዋል። ሕገ ወጥ የመሬት ወረራን ለመከላከል በተሠሩ ሥራዎች በ2017 በጀት ዓመት ብቻ 206 ሺህ ሕገ ወጥ ይዞታዎች ወደ ሕጋዊ ሥርዓት እንዲገቡ የተደረገ ሲሆን፣ ለ115 ሺህ ሰነድ-አልባ ይዞታዎች ሰነድ ተዘጋጅቷል። ባለፉት 5 ዓመታት በመንግሥት፣ በሪል ስቴት አልሚዎች እና በግል ቤት ሠሪዎች ትብብር ከ1.1 ሚሊዮን በላይ ቤቶች ተገንብተዋል። በተጨማሪም ማኅበረሰብን በማስተባበር 166,207 የዐቅመ ደካማ ቤቶች ተገንብተው ተላልፈዋል። ከደረጃ በታች የሆኑ የከተማ ቤቶች ድርሻም በ2013 ከነበረበት 75 በመቶ በ2017 ወደ 52 በመቶ ዝቅ እንዲል ተደርጓል። በሚቀጥሉት ዓመታት የከተማ መሬትን ምርታማነት ለመጨመር የይዞታ ማረጋገጫ ሥርዓት የሚጎለብት ሲሆን፣ የመሬት አያያዝ እና አጠቃቀም ይበልጥ ፍትሓዊ እንዲሆን እቅድ ተይዟል ። በከተሞች የሚታየውን የመኖሪያ ቤት እና የሥራ አጥነት ችግር ለመፍታት በትኩረት የሚሠራ ሲሆን፣ በሚቀጥሉት ዓመታት 2.2 ሚሊዮን ቤቶች እንዲገነቡ ይደረጋል። በከተሞች ያለው የቤት ሽያጭ እና የቤት ኪራይ አሠራር ገበያ-መር ሆኖ ፍትሓዊ የገበያ ሥርዓትን እንዲከተል ማድረግ ያስፈልጋል ። ከተሞች ከበካይ ነገሮች የጸዱ እንዲሆኑ ከከተማ ይዞታ ውስጥ 30 በመቶው የአረንጓዴ ልማት ቦታ ሆኖ እንዲጠበቅ እየተሰራ ነው ። የመንገድ፣ የትራንስፓርት፣ የንጹሕ ውኃ እና የመብራት አቅርቦት ተደራሽነትን ለማሳደግ ሰፊ ርብርብ ማድረግ ይገባል ።
በዜጎች ሕይወት ላይ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡ ፕሮጀክቶችን አጠናክረን እንቀጥላለን - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 22, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር 24/7 በመሥራት በዜጎች ኑሮ ላይ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡና ማኅበረሰቡ ጤናማ በሆኑ አካባቢዎች አገልግሎት ማግኘት የሚችልባቸውን ፕሮጀክቶች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ የዓድዋ የገበያ ማዕከል እና የትራንስፖርት ተርሚናልን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል፡፡ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ መንግሥት አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብ እና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን በሚመጥን መልኩ የመሠረተ ልማት ግንባታ ሥራዎችን አጠናክሮ ቀጥሏል። ከተማ አስተዳደሩ ቃል በገባው መሠረት ዜጎች ምቹ በሆነ አካባቢ የተቀላጠፈ አገልግሎት የሚያገኙባቸው በርካታ መሠረተ ልማቶች መገንባታቸውን አንስተዋል። ለአብነትም ምቹ የእንቅስቃሴ መንገዶችን ማስፋፋት፣ ሕዝቡ በጥሩ ሁኔታ ላይ ሆኖ የትራንስፖርት አገልግሎት የሚያገኝባቸውን ተርሚናሎች መገንባት እንዲሁም ዘመናዊ የመሸጫ የንግድ ሱቆችን ማጠናከር ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዛሬው ዕለትም የሕዝብን ክብር በሚመጥን መልኩ የተገነባው የዓድዋ የገበያ ማዕከልና የትራንስፖርት ተርሚናል መመረቁን የገለጹት ከንቲባዋ፤ ይህም የተቀናጀ አገልግሎትን ለማኅበረሰቡ ለመስጠት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር አስታውቀዋል። ከተማ አስተዳደሩ 24/7 በመሥራት በዜጎች የዕለት ተዕለት ሕይወት ላይ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡ ፕሮጀክቶችን በመሥራት ትጉህነቱን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዲዛይንና ግንባታ ሥራዎች ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር አያልነሽ ሀብተማርያም በበኩላቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ የሀገሪቱን የልማት ጉዞ የሚመጥኑና ለትውልድ አኩሪ የሆኑ በርካታ ፕሮጀክቶችን ገንብቶ ለአገልግሎት ማብቃቱን ገልጸዋል። በዛሬው ዕለት ለንግድ እንቅስቃሴ መዘመንና ለትራፊክ ፍሰት መሳለጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ የዓድዋ የገበያ ማዕከል እና የትራንስፖርት ተርሚናል፤ ሌሊትና ቀን በመሥራት ለአገልግሎት ክፍት መደረጉን ጠቁመዋል። ይህ የዓድዋ የገበያ ማዕከል እና የትራንስፖርት ተርሚናል ፕሮጀክት በውስጡ በርካታ የተሽከርካሪ ማቆሚያዎችን፣ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያዎችን፣ የተለያዩ ምርቶች መሸጫ ሱቆችንና ሌሎችንም ዘመናዊ የአገልግሎት መስጫዎችን እንደያዘ ጠቅሰዋል። የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ ያብባል አዲስ በበኩላቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ የትራንስፖርት ዘርፉን ለማሳደግ ዘርፈ-ብዙ የልማት ሥራዎችን አጠናክሮ እየሠራ መሆኑንና የዛሬው ተርሚናል ምርቃትም የዚህ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት የተከናወኑ የከተማ ልማት ሥራዎች ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ አድርገዋል
May 22, 2026 105
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የተከናወኑ የከተማ ልማት ሥራዎች ከተሞችን ለነዋሪዎች የተመቹ፣ ለጎብኚዎች ደግሞ ውብና ሳቢ እንዲሆኑ ማስቻሉን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ገለጹ። የከተማ ልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር ዜጎችን ከተረጂነት ወደ አምራችነት በማሸጋገር ረገድ በአፍሪካ ደረጃ አርአያነት ያለው መሆኑን ጠቅሰዋል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በርካታ የከተማ ልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። ለከተሞች ልማት ትኩረት በመሰጠቱ ለነዋሪዎች ምቹ፣ ለጎብኚዎች ደግሞ ውብና ሳቢ እንዲሆኑ መደረጉን ገልጸዋል። ለአብነትም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተተገበረው የኮሪደር ልማት፣ የከተሞችን ገጽታ ሙሉ በሙሉ ከመቀየር ባለፈ ለነዋሪዎች ምቹና ተስማሚ የአኗኗር ከባቢ መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡ የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክቶች አዲስ አበባን የአፍሪካ ተምሳሌትና ለቱሪዝም ፍሰት ምቹ ማድረግ መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ ይህ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተመዘገበው ታላቅ የልማት ስኬት፣ የነዋሪዎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በዘላቂነት የሚያረጋግጡ ዘመናዊ መሠረተ ልማቶችን በስፋት ማካተት መቻሉን ጠቅሰዋል። ጥራት ያላቸው ዘመናዊ የእግረኛ መንገዶችን በመገንባት ዜጎች በነፃነትና በደኅንነት እንዲንቀሳቀሱ ያስቻለ ሲሆን፣ ለተሽከርካሪዎችም ምቹና ደረጃቸውን የጠበቁ መንገዶች በመስራት የትራፊክ ፍሰቱ በእጅጉ እንዲቃለል ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም ፕሮጀክቱ የአካባቢ ጥበቃን፣ የአረንጓዴ ልማትንና የነዋሪዎችን ጤናማ የአኗኗር ዘይቤ ታሳቢ ያደረገ መሆኑ ተናግረዋል፡፡ ይህ ሁለንተናዊ የከተማ ልማት ሥራ የዜጎችን የዕለት ተዕለት ሕይወት በማሻሻል ረገድ የላቀ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡ መንግሥት ለከተሞች በሰጠው ትኩረት ለውጥ ከተመዘገበባቸው የልማት ሥራዎች አንዱ የሆነው የከተሞች ልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር፣ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ያሉ ዜጎችን ሕይወት በተግባር መቀየሩን ተናግረዋል። መርሃ ግብሩ በሰማንያ ስምንት ከተሞች የሚተገበርና 2 ነጥብ 5 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎችን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። ከተጠቃሚዎቹ መካከል 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚበልጡት ተመርቀው ወደ አምራችነት መሸጋገራቸውን ጠቅሰው፤ ቀሪዎቹ ደግሞ በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ውስጥ እንደሚሸጋገሩ አብራርተዋል። ይህ አሠራር ዜጎች በኢንተርፕራይዝ ደረጃ በመደራጀት ራሳቸውን ከመደገፍ ባለፈ፣ ለሌሎችም ተጨማሪ የስራ ዕድል እንዲፈጥሩ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው የከተማ ልማታዊ ሴፍቲኔት መርሃ ግብር ስኬታማነት በአፍሪካ ደረጃ ሞዴል የሆነና ሌሎች ሀገራትም ተሞክሮ እየወሰዱበት ያለ መሆኑን ተናግረዋል።
በፓርኩ ያለው የተሟላ መሰረተ ልማትና በመንግስት የሚደረገው ድጋፍ ባለሀብቱን መሳብ እያስቻለ ነው
May 22, 2026 108
ሀዋሳ፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ በይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ ያለው የተሟላ መሰረተ ልማትና በመንግስት የሚደረገው ድጋፍ አልሚ ባለሀብቶችን እየሳበ መሆኑ ተገለጸ። በፓርኩ የአዳዲስ ፋብሪካዎች ምረቃና የዕውቅና መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡ በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ሙዝና ቡናን በዘመናዊ መልኩ ዕሴት ጨምረው ለዓለም ገበያ የሚያቀርቡ ሁለት አዳዲስ ፋብሪካዎች በይፋ ሥራ ጀምረዋል። በመርሃ ግብሩ የተገኙት የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ኃላፊና የፓርኩ የቦርድ ሰብሳቢ መምሩ ሞኬ፤ የኢኮኖሚው መሰረት የሆነውን የግብርና ምርት ዕሴት ጨምረው ለውጭ ገበያ ለሚያቀርቡ ኢንዱስትሪዎች መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። በዚህ በኩል የይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ በአጭር ጊዜ ውስጥ በምርቶች ላይ ዕሴት በመጨመር ውጤታማ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለበርካታ የአካባቢው አርሶ አደሮችና ወጣቶች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የውጭ ምንዛሪን በማስገኘት በኩል ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ለዚህ ደግሞ አስፈላጊው መሰረተ ልማት የተሟላለት ፓርኩ ለባለሀብቶች ምቹ መሆኑ ዋነኛ ምክንያት መሆኑን አብራርተዋል። የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኃይሉ የተራ፤ ፓርኩ ሥራ ከጀመረባቸው ባለፉት አምስት ዓመታት ወዲህ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በውጭ ምንዛሪ ግኝት፣ በተኪ ምርት፣ በገበያ ትስስርና በሥራ ዕድል ፈጠራ ከፍተኛ ውጤት እያስገኘ ነው ብለዋል። በፓርኩ የግብርና ምርቶችን በማቀነባበር ሥራ ላይ ለመሰማራት ዛሬ ሥራ የጀመሩትን ጨምሮ በአጠቃላይ 10 ኩባንያዎች በምርት ሂደት ላይ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በዚህም እስካሁን ከ26ሺህ ለሚልቁ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቅሰው፤ ፓርኩ ባለው የመሰረተ ልማት ምቹነት፣ በመንግስት ቀጣይነት ያለው ድጋፍና ክትትል ታክሎበት የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል። በዕለቱ በይፋ ሥራ ከጀመሩት ፋብሪካዎች መካከል የኤፔክስ ማኑፋክቸሪንግና ትሬዲንግ መስራችና ዋና ሥራ አስኪያጅ መስፍን ተፈራ ኩባንያቸው ሙዝን በዘመናዊ መንገድ በችፕስ መልክ ለገበያ ለማቅረብ ስራ መጀመሩን ተናግረዋል። የፋብሪካው ሥራ መጀመር በክልሉና በአጎራባች አካባቢዎች በስፋት በሙዝ አምራችነት ለተሰማሩ አርሶ አደሮች ተጨማሪና አስተማማኝ ገቢ ይዞ መምጣቱን ጠቅሰው፤ በአሁኑ ወቅት ከ60ሺህ ከሚሆኑ አምራቾች ጋር የገበያ ትስስር መፈጠሩን አመልክተዋል። ኩባንያው ምርቶቹን ከሀገር ውስጥ ገበያ ባለፈ ወደ ውጭ እንደሚልክም ገልጸዋል። ሌላው በቡና ማቀነባበር ሥራ ላይ የተሰማራው የቻይናው 'መይመይ ኮፊ ፕሮሰሲንግ' ኩባንያ ተወካይ ሚስተር ጄ ሶን፤ በፓርኩ በተፈጠረው ምቹ ሁኔታና መሰረተ ልማት ተስበው ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። ፋብሪካው ቡናን ከአርሶ አደሩ ማሳ ቀጥታ በመረከብ፤ ማጠብና መፍጨት ጀምሮ የተጠናቀቀ ዝግጁ ቡና ለዓለም አቀፍ ገበያ እስከማቅረብ ድረስ ያለውን ሙሉ ሂደት እዚያው ፓርኩ ውስጥ እንደሚያከናውን ገልጸዋል። በዕለቱ ዕውቅና ከተሰጣቸው ባለሀብቶች መካከል የ'ጎልደን' የአቮካዶ ዘይት ፋብሪካ ባለቤት ወይዘሮ ይርጋለም አስፋው ፋብሪካው ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ ብቻ 16 ኮንቴይነር የአቮካዶ ዘይት ምርት ወደ ውጭ ሀገር መላክ ችሏል ብለዋል። ዛሬ የተሰጣቸው ዕውቅና በቀጣይ ይበልጥ ጠንክረው እንዲሰሩ ትልቅ መነቃቃት የፈጠረላቸው መሆኑን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መካከል ያለው የላቀ ትብብር ለኢትዮጵያውያን ሰፊ የሥራ ዕድል ፈጥሯል
May 22, 2026 119
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መካከል ያለው የላቀ ትብብር ለኢትዮጵያውያን ሰፊ የሥራ ዕድል እየፈጠረ መሆኑን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምሥራቅ፣ የእስያና ፓስፊክ ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር ጄነራል አምኃ ኃይለጊዮርጊስ ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መካከል ያለውን የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር ለማጠናከር ያለመው የዱባይ-ኢትዮጵያ ቢዝነስ ትስስር ፎረም በአዲስ አበባ ተካሂዷል፡፡ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምሥራቅ፣ የእስያና ፓስፊክ ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር ጄነራል አምኃ ኃይለጊዮርጊስ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የዱባይ-ኢትዮጵያ ቢዝነስ ትስስር ፎረም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ትብብር ለማጠናከር ወሳኝ ነው፡፡ ኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ያላቸው ሁለንተናዊ ግንኙነት እየጎለበተ መምጣቱን ገልጸው፤ ፎረሙ የጋራ ተጠቃሚነትን ያረጋግጣል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ስትራቴጂያዊ የንግድና ኢንቨስትመንት መዳረሻ ናት ያሉት ምክትል ዳይሬክተር ጄነራል አምኃ፤ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ ወሳኝ አጋር መሆኗንም ገልጸዋል፡፡ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ የውጭ ንግድ መዳረሻ መሆኗን ገልጸው፤ 169 ኩባንያዎች በኢትዮጵያ የተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ተሰማርተው ይገኛሉ ብለዋል፡፡ እንደ አውሮፓውያን የዘመን ቀመር በ2018 ጀምሮ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው ግንኙነት በጥልቀትና በስፋት እያደገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ትብብሩም የሁለቱ ሀገራት የጋራ ብልጽግናን እውን ሊያደርግ በሚችል የጋራ እሴቶች ላይ የተመሠረተ መሆኑን አንስተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ብዝኃና እምቅ የንግድና ኢንቨስትመንት አቅም፣ ለኢንቨስትመንት የተመቹ አሠራሮች እንዳሏት በማንሳት፤ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ኩባንያዎች ዕድሉን ሊጠቀሙበት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ በኢትዮጵያ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ኤምባሲ የኢኮኖሚ፣ ፖለቲካና ሚዲያ ክፍል ኃላፊ ራሼድ አብዱላ አልሸሂ፤ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች የምትከተለው የዓለም አቀፍ የቢዝነስ ትስስር ሞዴል ኢትዮጵያንም ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል፡፡ በሌላ በኩል ሀገሪቱ ያላትን ሰፊ የገበያ አማራጭና እየተገበረች ያለውን የኢኮኖሚ ማሻሻያ በመጥቀስ፣ ለንግድና ኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎችን እየፈጠረች መሆኑን አስገንዝበዋል። የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች በታዳሽ ኃይል፣ በግብርናና ኢንዱስትሪ እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ትብብር የምታጠናክርበት መድረክ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ኢንጂነር አበበ ጉርሜሳ በበኩላቸው፤ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ለምክር ቤቱ አባል ኩባንያዎች ዋነኛ መዳረሻና መገኛ መሆኗን ገልጸዋል፡፡ የዱባይ ኩባንያዎች በዲጂታል አገልግሎት፣ በቱሪዝምና በሌሎችም ዘርፎች ያላቸው ተሳትፎ ለሁለቱ ሀገራት ኩባንያዎች ትብብር መሠረት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አበባና የዱባይ የቢዝነስ ኩባንያዎች በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ በጋራ በመሰማራት ትብብራቸውን እንዲያጠናክሩ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በክልሉ በለውጡ ዓመታት ሕዝቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተጠናቀው ለአገልግሎት በቅተዋል
May 22, 2026 105
ሸገር፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ባለፉት የለውጥ ዓመታት ሕዝቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ሰዓዳ አብዱረህማን ገለጹ። በሸገር ከተማ አስተዳደር በኮዬ ፈጬና በገላን ክፍለ ከተሞች የተገነቡ የ“ቡኡራ ቦሩ” ቅድመ መደበኛ እና የአንደኛ ደረጃ ሞዴል ትምህርት ቤቶች፣ የንጹህ መጠጥ ውኃ እንዲሁም የሕዝብ መናፈሻ ፓርኮች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። በምርቃቱ ሥነ ሥርዓት ላይ የተገኙት የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ሰዓዳ አብዱረህማን እንደገለጹት፤ በክልሉ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የሕዝቡን መሠረታዊ ጥያቄዎች የመለሱ በርካታ የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነት በመገንባታቸው የሕብረተሰቡ ተጠቃሚነት ሊረጋገጥ ችሏል። በተለይም በእውቀትና ቴክኖሎጂ የዳበረ፣ አገር ተረካቢ ትውልድ ለማፍራት ጊዜው የሚጠይቀውን ዘመናዊ ትምህርት ተደራሽ ከማድረግ አኳያ ሰፊ ሥራ መሠራቱን አብራርተዋል። በሸገር ከተማ በኮዬ ፈጬና ገላን ክፍለ ከተሞች ዛሬ የተመረቁት ትምህርት ቤቶች፣ የመጠጥ ውኃና የፓርክ ፕሮጀክቶች የዚሁ ሰፊ እንቅስቃሴ ማሳያ መሆናቸውን የገለጹት አፈ ጉባኤዋ፤ መምህራን ትውልዱን በማነጽ ረገድ የበኩላቸውን ኃላፊነት መወጣት እንዳለባቸው አሳስበዋል። ሕዝቡም ከመንግሥት ጎን በመሆን ሁለንተናዊ ተሳትፎውን አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ጥሪ አቅርበዋል። የሸገር ከተማ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤ በሸገር ከተማ ባለፉት ሦስት ዓመታት የከተማዋን ሀብት በአግባቡ በማስተዳደር የነዋሪውን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት ተደርጎ መሠራቱን ገልጸዋል። በከተማዋ በርካታ የልማት ፕሮጀክቶችን በመገንባት የሕብረተሰቡ የልማት ጥያቄ በተሟላ መልኩ እየተመለሰ መሆኑንም አክለዋል። ባለፉት ሦስት ዓመታት በከተማዋ መሠረተ ልማቶችን ከመዘርጋት፣ የከተማዋን ገቢ ከማሳደግ፣ የጤና ተቋማትን ከመገንባትና ኢንቨስትመንትን ከማስፋፋት አኳያ ተጨባጭ ሥራዎች መከናወናቸውን ከንቲባው አንስተዋል። በተለይም የከተማዋን አርሶ አደር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ሼዶችና የገበያ ማዕከላት ግንባታቸው ተጠናቀው ለአርሶ አደሮቹ መተላለፋቸውን ተናግረዋል። በተያዘው በጀት ዓመት ከተማ አስተዳደሩ 448 የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለመገንባት አቅዶ እስካሁን 338 የሚሆኑ ፕሮጀክቶች ማጠናቀቅ መቻሉን ገልጸዋል። የከተማ አስተዳደሩ ሳይመሠረት በፊት በትምህርት ገበታ ላይ የነበሩ ተማሪዎች ቁጥር ከ100 ሺህ የማይበልጥ የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ላይ ከ400 ሺህ በላይ ማድረስ መቻሉን ከንቲባው ገልጸዋል። በተጨማሪም በገላን ክፍለ ከተማ ተገንብቶ የተመረቀው የንጹህ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት ከ33 ሺህ በላይ የአካባቢው ነዋሪዎችን ንጹሕ የመጠጥ ውኃ ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑ ታውቋል። የኮዬ ፈጬ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ኩመላ ሂርጳ፤ በክፍለ ከተማው በበጀት ዓመቱ የታቀዱ 25 የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶችን በመንግሥት በጀትና በሕዝብ ተሳትፎ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ዛሬ በቱሉ ዲምቱ ወረዳ ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት ትምህርት ቤቶች በክፍለ ከተማው ከተከናወኑት ስኬታማ ሥራዎች መካከል ተጠቃሽ መሆናቸውን የገለጹት ኃላፊው፤ ፕሮጀክቶቹ የትምህርት ጥራትና ተደራሽነትን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ የአካባቢው ማኅበረሰብ ልጆቹን በአቅራቢያው ለማስተማር እንደሚያስችለው ገልጸዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጠናክሮ ቀጥሏል
May 22, 2026 77
አምቦ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች በጥራትና በብዛት እየተገነቡ መሆናቸውን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በዞኑ ኤጀሬና ወልመራ ወረዳዎች የተገነቡ የኮሪደር ልማት፣ የከፍተኛ ፍርድ ቤት ህንፃ እና ሌሎች የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀዋል። በፕሮጀክቶቹ ምረቃ ስነ-ስርዓት ላይ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታን ጨምሮ የዞኑና የወረዳዎቹ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል። ዋና አስተዳዳሪው አቶ ዲዳ ጉደታ በወቅቱ እንደገለጹት፤ መንግስት የገባውን ቃል በመተግበር የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ እየመለሰ ይገኛል። በዞኑም ባለፉት የለውጥ ዓመታት ለረጅም ጊዜ የህብረተሰቡ ጥያቄ ሆነው የቆዩትን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና የሌሎች ዘርፎች ጥያቄዎችን መመለስ መቻሉን ተናግረዋል። ወደፊትም የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ የልማት ስራዎች በጥራትና በብዛት የመገንባቱ ስራ ይቀጥላል ብለዋል። የኤጄሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አዱኛ ብሩ በበኩላቸው፤ በወረዳው ለአገልግሎት ከበቁ የልማት ፕሮጀክቶች መካከል የሁለት ኪሎ ሜትር የከተማ ኮሪደር ልማት፣ የወተት ላሞች እርባታና የከብት ማደለቢያ ማዕከላት እንደሚገኙበት ገልጸዋል። በወረዳው ዛሬ ለምርቃት የበቁት እነዚህ ፕሮጀክቶች በህብረተሰቡ ተሳትፎና በመንግሥት በጀት በአጠቃላይ 122 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በተመሳሳይ የወልመራ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጋሪ በበኩላቸው፤ አካባቢው የበጋ ስንዴን ጨምሮ የተለያዩ የሰብል እህሎች በስፋት የሚመረቱበት መሆኑን ገልጸው፤ ዛሬ የተመረቀው የ13 ነጥብ 2 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ወረዳውን ከቀበሌዎች ጋር የሚያገናኝ በመሆኑ አርሶ አደሮች ምርታቸውን በቀላሉ ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እንደሚረዳቸው አስረድተዋል። ዛሬ ከተመረቁት ፕሮጀክቶች መካከል የከብትና የዶሮ እርባታ ማዕከላት፣ ባለ ሶስት ወለል የወረዳ ፍርድ ቤት ህንፃ እና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተጨማሪ ክፍሎች ይገኙበታል ብለዋል። እነዚህ ፕሮጀክቶች በመንግሥት በጀትና በህብረተሰቡ ተሳትፎ በአጠቃላይ 250 ሚሊዮን ብር ወጪ የተሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። የወልመራ ወረዳ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ስሪኔሳ ኩማላ፤ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው ባለ ሶስት ወለል የፍርድ ቤት ህንጻ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋ የህግ አገልግሎት ለመስጠት ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ተናግረዋል። የኤጀሬ እና የወልመራ ወረዳ ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ የልማት ጥያቄዎቻቸው ለብዙ ዓመታት መልስ ሳያገኙ መቆየታቸውን አስታውሰው፤ አሁን ላይ ለተገነቡላቸው ፕሮጀክቶች የተሰማቸውን ደስታ በመግለጽ አስፈላጊውን እንክብካቤ እንደሚያደርጉ አረጋግጠዋል።
መንግስት ሰላምን ከማስከበር ጎን ለጎን ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ተግባራትን አከናውኗል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
May 22, 2026 58
ባህርዳር፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል መንግስት ሰላምን ከማስከበር ጎን ለጎን ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ በርካታ የልማት ተግባራትን አከናውኗል ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለፁ። "ኢትዮጵያን ወደ ተምሳሌት ሀገር" በሚል መሪ ሃሳብ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫን አስመልክቶ ከባህርዳር ከተማ አስተዳደር ከተውጣጡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር የውይይት መድረክ ተካሄዷል። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የለውጡ መንግስት ፕሮጀክቶችን በማቀድና ፈጥኖ በመጨረስ ለሀገሪቱ አዲስ ልምምድ አበርክቷል። በቱሪዝም፣ በማዕድን ፣ በግብርና ፣ በኢንዱስትሪና ሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች ተግባራዊ የተደረጉ ፕሮጀክቶችም ለአገር እድገት መሰረት የሆኑና የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ያረጋገጡ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለዚህም መላውን ህዝብ በማሳተፍ የክልሉን ሰላም ለማረጋገጥ የተደረገው ጥረት ውጤት እያስገኘ በመምጣቱ ለልማት ስራው ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አስረድተዋል። በቀጣይም ህዝቡን በማስተባበር በልማትና በሰላም ማስፈን ስራዎች ለማረባረብ እንደሚሰራ ጠቁመው ምርጫውን በሰላም ለማጠናቀቅ ህዝቡ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት እንዲወጣም አሳስበዋል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው በበኩላቸው፤ ሀገር ጸንታ የምትቀጥለውና የምትሻገረው የሚያጋጥሙ ችግሮችን በንግግርና በውይይት መፍታት ሲቻል ነው ብለዋል። የሚገጥሙ ችግሮችን በውይይት እና በመግባባት መፍትሔ በመስጠት የሚካሄዱ የልማት ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ለማድረግ የጎላ ፋይዳ እንደሚኖረውም አስረድተዋል። ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫም ፍፁም ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሁሉም ህብረተሰብ የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ብለዋል። ምርጫውን ነፃ፣ ፍትሃዊ፣ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅና የባህር ዳር ከተማን ተመራጭ የቱሪዝም፣ የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ከተማ ለማድረግ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በመድረኩም የክልሉና የባህርዳር ከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሃገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶችና ሴቶች ታድመዋል።
በዞኑ ለመኸር ወቅት የተዘጋጀ ከ10 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ እየዋለ ነው
May 22, 2026 91
ደብረ ብርሃን ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ለመኸር ወቅት እርሻ ለምርት ማሳደጊያነት በአርሶ አደሮች የተዘጋጀ ከ10 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ጌታነህ ተክለማሪያም ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የተፈጥሮ ማዳበሪያ የአፈር ለምነትንና እርጥበትን በመጨመር ለምርት እድገት የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። በዚህም በዞኑ ለ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት በአርሶ አደሮች የተዘጋጀ ከ10 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑን ተናግረዋል። በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅቱ ከ363ሺህ በላይ አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን አመልክተዋል። እስካሁንም ሰባት ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ የሚሆነው የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማሳን ደጋግሞ በማረስ ከአፈር ጋር በመቀላቀል ጥቅም ላይ መዋሉን ተናግረዋል። በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅቱ ከተሳተፉ አርሶ አደሮች መካከልም አቶ ኩራ ተሾመ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት የተፈጥሮ ማዳበሪያን አዘጋጅተው በመጠቀማቸው የማሳቸው ለምነት መጨመሩ የሰብል ምርታቸውን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። ዘንድሮም የተፈጥሮ ማዳበሪያ በማዘጋጀት አንድ ሄክታር ተኩል መሬታቸውን በቢራ ገብስ፣ በአተርና ባቄላ ዘር ለመሸፈን እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። አርሶ አደር ገበየሁ ማንደፍሮ በበኩላቸው፤ ባለፉት አመታት የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘጋጅተው በመጠቀማቸው ምርታቸውን ከማሳደግ ባለፈ ለፋብሪካ ማዳበሪያ ግዥ የሚያወጡትን ወጭ መቀነስ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። ዘንድሮም ለመኸር ወቅት እርሻ የሚሆናቸውን የተፈጥሮ ማዳበሪያ ከቅጠላቅጠል፣ ከእንስሳትና ሰብል ተረፈ ምርት በማዘጋጀት ሁለት ሄክታር መሬታቸውን በተለያዩ ሰብሎች በዘር የመሸፈን ስራ መጀመራቸውን ተናግረዋል። በዞኑ በ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት ከ563 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰብል በማልማት 20 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑ ታውቋል።
በክልሉ በማዕድን ዘርፍ ከ246 ነጥብ 1 ሚሊየን ዶላር በላይ ተኪ ምርት ማምረት ተችሏል
May 22, 2026 89
ባህርዳር፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በተያዘው በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት በማዕድን ዘርፍ ከ246 ነጥብ 1 ሚሊየን ዶላር በላይ የሚያወጡ ተኪ ምርቶች መመረታቸውን የክልሉ ማዕድን ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ፖሊሲው ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው አምስት ዘርፎች አንዱ የማዕድን ሃብትን በማልማት ለሀገር እድገትና ብልጽግና ለማዋል እየተሰራ ነው። የቢሮው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ዝናው አበበ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ያለውን እምቅ የማዕድን ሃብት በጥናት በመለየት በዘመናዊ እና ባህላዊ መንገድ እየለማ ይገኛል። በክልሉ የሚገኙ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን በማሳተፍ በተያዘው ዓመት 18 የማዕድን ሃብት የጥናትና ምርምር ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ርክክብ መፈፀሙን ገልፀዋል። በዚሁ መሰረትም የኮንስትራክሽን፣ ብረትና ብረት ነክ፣ የከበሩ ማዕድናት፣ ለኃይል አቅርቦትና መሰል አገልግሎት የሚውሉ ማዕድናት በክልሉ እንደሚገኙ ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል። የጥናቱን ግኝት ለባለሃብቶች በማቅረብ ወደ ልማት እንዲገቡ በተደረገው ጥረት ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ 169 ፕሮጀክቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በዚህም ከ2 ነጥብ 4 ሚሊየን ቶን በላይ ጅብሰም፣ ላይም ስቶን፣ ሲልካሲድ፣ ድንጋይ ከሰል፣ እምነ በረድ፣ ግራናይትና መሰል ምርቶችን በማምረት ከ246 ነጥብ 1 ሚሊየን ዶላር በላይ ግምታዊ ዋጋ ያላቸው ተኪ ምርቶችን ማምረት መቻሉን ገልጸዋል። እንዲሁም ከ18 ሺህ 500 ኪሎ ግራም በላይ እሴት የተጨመረበትና ጥሬ ኦፓልና ወርቅ ለማዕከላዊ ገበያ በማቅረብ ከ13 ሚሊየን ዶላር የሚጠጋ የውጭ ምንዛሬ ማስገኘት መቻሉን አስረድተዋል። በዘርፉ በተደረገ እንቅስቃሴም ለ33 ሺህ ወገኖች የስራ ዕድል በመፍጠር በኢኮኖሚ የላቀ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ እንዳስቻለም ተናግረዋል። የማዕድን ዘርፉ በተለይም የኮንስትራክሽን ዘርፉን ግብዓት ሙሉ በሙሉ መሸፈን እንዳስቻለ ጠቅሰው፤ ይህም በከተሞች እያደገ የመጣውን የግንባታ እንቅስቃሴ እንዲፋጠን ማገዙን አረጋግጠዋል። በክልሉ 25 በመቶ የሚሸፍን የስነ ምድር ካርታ ጥናት የተካሄደ ሲሆን የ51 ማዕድናት የስርጭት የቦታ ልየታ ስራ መከናወኑንም ጨምረው አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የስምንት አስርት ዓመታት ወርቃማ ስምና ዝና የአፍሪካ የትስስር ተምሳሌት እንዲሆን አስችሎታል
May 22, 2026 137
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የስምንት አስርት ዓመታት ወርቃማ ስምና ዝና ጉዞ የአፍሪካ የትስስር ተምሳሌት እንዲሆን ማስቻሉን እንግሊዛዊ ዲፕሎማት ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ''አዲሱ የአፍሪካ መንፈስ” የሚለው ሃሳብ የአህጉሪቱን የዕድገትና ብልፅግና ጉዞ በማፋጠን አፍሪካን ከቀሪው ዓለም የሚያገናኝበት መገለጫው እንዲሆን አድርጎታል። በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ የኮሙኒኬሽንና የሶፍት ፓወር ክፍል ኃላፊ ጄሚ ማንዝብሪጅ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም አቀፍ የበረራ አገልግሎት መለያ ዕሴት የገነባ ተቋም ነው። የአየር መንገዱ ዘመናዊ አውሮፕላኖችና የበረራ ምልክት የተደራሽነት አድማሱን በማስፋት አፍሪካን ከቀሪው ዓለም የሚያገናኝበትን ዕድል እንደፈጠረለት ገልጸዋል። አፍሪካን ከቀሪው ዓለም በማገናኘት የሚሰጠው አስደናቂ የበረራ አገልግሎት ከሌሎች አየር መንገዶች ልዩ እንደሚያደርገውም ተናግረዋል። ዓለም አቀፍ የበረራ ተደራሽነቱ የአየር መንገዱን አውሮፕላኖች መለያ ምልክት በማጉላት ተምሳሌታዊ አገልግሎት የሚሰጥበትን ዕድል እንደፈጠረ አንስተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለስምንት አስርት ዓመታት በገነባው ወርቃማ ስም አፍሪካን ከዓለም በማገናኘት ቁልፍ ሚና እየተወጣ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም የዓለም ማህበረሰብ የአፍሪካን የቱሪዝም፣ የንግድ፣ ኢንቨስትመንትና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። በአፍሪካ የአቪየሽን ኢንዱስትሪ የኢትዮጵያ አየር መንገድ መሪ ተዋናይነቱን የሚያጎለብትበትን የዕውቀትና ልምድ ልውውጥ ማዕከል እንዲሆን ማስቻሉንም ገልጸዋል። የአየር መንገዱ ምቹ የበረራ መስተንግዶ ደንበኞች የኢትዮጵያንና የአፍሪካን የመስህብ መዳረሻ የሚጎበኙበትን ዕድል እንደፈጠረ ጨምረው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ሁሉን አቀፍ ግንኙነት የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብሩን እያጠናከረ ነው
May 22, 2026 157
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያና የተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች ሁሉን አቀፍ ግንኙነት የሁለቱን ሀገራት የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር እያጠናከረ መምጣቱን በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በዱባይ የንግድ ምክር ቤት የተዘጋጀው የዱባይ - ኢትዮጵያ ቢዝነስ ትብብር ፎረም በአዲስ አበባ ተካሂዷል፡፡ በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ኢትዮጵያን ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት መዳረሻ አድርጓታል፡፡ ኢትዮጵያ በቀጣናው ምቹ የኢንቨስትመንት ሥነ-ምህዳርና የጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ ያላት ስትራቴጂያዊ የቢዝነስ መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የወጣቶች ምድር፣ የአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን አፍሪካውያን የገበያ መዳረሻ እንዲሁም የብቁ የሰው ኃይል መገኛ ናት ብለዋል፡፡ ሀገራዊ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ለንግድና ኢንቨስትመንት እንቅፋት የሆኑ አሠራሮችን በማስወገድ ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢ መፍጠር ማስቻሉን ገልጸዋል፡፡ በተሟላ መሠረተ ልማት ፈጣንና ቀልጣፋ የንግድ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ገልጸው፤ በኢንዱስትሪ ፓርኮች የአንድ ማዕከል አገልግሎትን የሚያስችል አሠራር ተዘርግቷል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የዓለም ግዙፉን አየር መንገድ እየገነባች መሆኑን በማንሳት፤ የሎጂስቲክስ አገልግሎቱን በማሳለጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ አዎንታዊ ተፅዕኖ ያለው ሥራ እያከናወነች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መካከል ያለው ሁለንተናዊ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መሆኑን የገለጹት አምባሳደር ጀማል (ዶ/ር)፤ የሁለቱ ሀገራት መሪዎች ትብብሩ በጽኑ መሠረት ላይ እንዲገነባ አድርገዋል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ሁለንተናዊ ግንኙነት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች ኩባንያዎች የቴክኖሎጂ አቅም የተሻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት አጋዥ መሣሪያ ይሆናሉ ብለዋል፡፡ መንግሥት ለንግድና ኢንቨስትመንት ዝግጁ መሆኑን በመጥቀስ፤ ምቹ የሥራ አካባቢ መፍጠር እንደተቻለ ገልጸዋል፡፡ የዱባይ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዚዳንትና ዋና ሥራ አስፈጻሚ መሐመድ አሊ ራሼድ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ወሳኝ የንግድ፣ ኢንቨስትመንትና የገበያ መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በወሳኝ ስትራቴጂያዊ መልክዓ ምድር እና በአፍሪካ ግንባር ቀደም የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ትገኛለች ብለዋል፡፡ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች እና ኢትዮጵያ ያላቸው የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር እያደገ መምጣቱን በመጥቀስ፤ የዱባይ ኩባንያዎች ኢትዮጵያን መዳረሻቸው እያደረጓት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህ ዓመት እስከ መጋቢት መጨረሻ ድረስ አንድ ሺህ 676 በሥራ ላይ ያሉ የኢትዮጵያ ኩባንያዎች በዱባይ ንግድ ምክር ቤት አባልነት ተመዝግበዋል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኩባንያዎች በንግድ፣ ሪል-ስቴት፣ ሎጂስቲክስና መሰል ዘርፎች መሰማራታቸውን በመጥቀስ፤ በኢትዮጵያ እና ዱባይ መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ 6 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት አይናለም አባይነህ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያና በተባበሩት ዓረብ ኤምሬቶች መካከል ያለው ዲፕሎማሲያዊ ትብብር የግሉን ዘርፍ ንግድና ኢንቨስትመንት እያነቃቃ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የሁለቱ ሀገራት ትብብር ወደ ስትራቴጂያዊ አጋርነት ደረጃ እየተሸጋገረ መሆኑን ገልጸው፤ የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ሪፎርም የወጪ ንግድን፣ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን እንዲሁም ዓለም አቀፋዊና ቀጣናዊ ትብብርን አሳድጓል ብለዋል፡፡ በመሆኑም የዱባይና የኢትዮጵያ ኩባንያዎች በትብብር በመሥራት በኢትዮጵያ ያለውን እምቅ የኢንቨስትመንት አቅም ሊጠቀሙበት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
ኢንዱስትሪ ፓርኩ ወደ ውጭ ከላከው የአቮካዶ ዘይት ምርት ከ2 ነጥብ 5 ሚሊየን ዶላር በላይ ገቢ አገኘ
May 22, 2026 146
ሀዋሳ፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦ ይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ለአውሮፓ ሀገራት ከላከው የአቮካዶ ዘይት ምርት ከ2 ነጥብ 5 ሚሊየን ዶላር በላይ ገቢ ማግኘቱን የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን አስታወቀ፡፡ የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሀይሉ የተራ፤ በክልሉ የኢንዱስትሪ ምርታማነትንና የገቢ አቅምን የማሳደግ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም በተለይ በይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ ወጭና ተኪ ምርቶችን በብዛትና በጥራት ለማምረት ትኩረት መሰጠቱን አንስተዋል። በኢንዱስትሪ ፓርኩ ኢንቨስት ለማድረግ ውል ከፈፀሙ 34 ድርጅቶች መካከል አሥሩ በምርት ሂደት ላይ ይገኛሉ ብለዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ለአውሮፓ ሀገራት ከተላከ የአቮካዶ ዘይት ምርት ብቻ ከ2 ነጥብ 5 ሚሊየን ዶላር በላይ ገቢ ማግኘቱን ተናግረዋል። በኢንዱስትሪ ፓርኩ የግብርና ምርቶችን በማቀነባበር ለሀገር ውስጥ ገበያ በማቅረብ ላይ የተሰማሩ አልሚዎችም ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሬ ማዳን ችለዋል ብለዋል። ፓርኩ የተሟላ መሰረተ ልማትና በዩኒየኖች በኩል ከአርሶ አደሩ ጥሬ ምርት መሰብሰብ የሚያስችል የተደራጀ ተቋማዊ አሰራር እንዳለው ያነሱት ሥራ አስፈጻሚው፣ በዘርፉ ለመሰማራት የሚፈልግ ባላሀብት ዕድሉን እንዲጠቀም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ወደ ሥራ ከገባ አንድ ዓመት የሆነውና በአቮካዶ ዘይት የተሰማራው የኢትዮ ፍሩት ፋብሪካ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ደጀኔ ጉታ በበኩላቸው ወደ 500ሺህ የአሜሪካን ዶላር ገቢ ያስገኘ ምርት ወደተለያዩ የአውሮፓ ገበያዎች መላካቸውን ተናግረዋል፡፡ ፓርኩ የተሟላ መሰረተ ልማት እንዳለው ገልጸው ወቅታዊውን የነዳጅ አቅርቦት ችግር ለመፍታት መንግስት እያደረገ ያለውን ድጋፍ አድንቀዋል፡፡ የዋይ.ቢ.ኤም የአቮካዶ ዘይት ፋብርካ ሥራ አስኪያጅ ፀጋአብ መለሰ በበኩላቸው ባለፉት አራት ዓመታት ከ8 ሚሊየን በላይ የአሜሪካን ዶላር ገቢ ያስገኘ ምርት ለውጭ ገበያ ከፋብሪካው መላኩን ገልጸዋል፡፡ ተግባሩን በማጠናከርም በተያዘው የምርት ወቅት ከ2 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር በላይ ገቢ የሚያስገኝ የአቮካዶ ዘይት ወደ አውሮፓ ገበያ ለመላክ እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ፓርኩ የተሟላ መሰረተ ልማት ያለው መሆኑ፣ የመንግስት ድጋፍና ክትትል እንዲሁም በአካባቢው ያለው የአቮካዶ ምርት አቅርቦት በስራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ እያገዛቸው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በፓርኩ አስፈላጊ መሰረተ ልማቶች ከመሟላታቸው ባለፈ በአካባቢው ጥሬ ምርትና የሰው ሀይል በበቂ ሁኔታ መኖሩ ለነባሩም ሆነ አዲስ በዘርፉ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ገልጸዋል። በ2012 ዓ.ም ወደ ሥራ የገባው የይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ በ294 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ ሲሆን የግብርና ምርቶች ማቀነባበር ዘርፍ ለሚሰማሩ አልሚ ባለሀብቶች አስፈላጊ መሰረተ ልማቶች የተሟሉለት ነው፡፡
ፕሮጀክቶች በፍጥነትና በጥራት ተገንብተው ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል-አቶ ኦርዲን በድሪ
May 22, 2026 103
ሀረር፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በሀረሪ ክልል የልማት ፕሮጀክቶች በፍጥነትና በጥራት ተገንብተው ተገቢውን አገልግሎት እንዲሰጡ ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ አቶ ኦርዲን በድሪ በክልሉ እየተገነቡ የሚገኙትን የሞዴል 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤትና ሌሎች የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። በዚህ ወቅትም ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት፣ በግንባታ ላይ የሚገኙ ፕሮጀክቶች በአሁኑ ወቅት በተሻለ አፈፃፀም ላይ ይገኛሉ። በተለይም የሞዴል 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቱ መገንባት የክልሉን የትምህርት ጥራትና ተደራሽነት የበለጠ በማሳደግ ረገድ ፋይዳው የላቀ ነው ብለዋል። በዘመናዊ ትምህርት የታነፀና በእውቀት የበለፀገ ሀገር ተረካቢ ትውልድን በማፍራት ረገድ ያለው አስተዋጽኦ የላቀ መሆኑን ነው ያነሱት። በቀጣይም ፕሮጀክቶቹ በፍጥነትና በጥራት ተጠናቀው ለክልሉ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት የድርሻቸውን እንዲወጡ ለማስቻል ተገቢው ክትትልና ድጋፍ እንደሚደረግ አረጋግጠዋል።
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የበጋ ስንዴ ልማት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የሚደረገውን ጉዞ እያገዘ ነው
May 22, 2026 84
ጭሮ፤ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የስንዴ ሰብል በበጋ መስኖ በማልማት እየተገኘ ያለው ውጤት፣ ማኅበረሰቡን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር የተጀመረውን ጥረት በከፍተኛ ደረጃ እያገዘ መሆኑን የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ፅህፈት ቤት ገለፀ። በፅህፈት ቤቱ የስንዴ ልማት ባለሙያ የሆኑት አቶ ሀቢብ አብዱልከሪም ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ ከ100 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በልማቱ ተሰማርተው በሚያገኙት ገቢ የኑሮ ለውጥ ማምጣት ችለዋል። ከዚህ ቀደም በበቆሎና በሌሎች ሰብሎች ይሸፈን የነበረ እንዲሁም ለግጦሽ ይውል የነበረ ከ40 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአሁኑ ወቅት በበጋ መስኖ ስንዴ እየለማ መሆኑን አመልክተዋል። በዚህ ወቅት ዓመታዊ ምርት ከ1 ሚሊዮን 300 ሺህ ኩንታል በላይ የደረሰ ሲሆን በአጠቃላይ ባለፉት አምስት ዓመታት ወደ 6 ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ምርት ተሰብስቧል ብለዋል። ባለሙያው አክለውም፣ አርሶ አደሩ የውሃ መሳቢያ ሞተሮችንና የግብርና ግብዓቶችን በስፋት መጠቀም መቻሉ ለምርት መጨመር ዋነኛ አስተዋፅዖ ማበርከቱን አብራርተዋል። የቦኬ ወረዳ አስተዳደር ፅህፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ሳሚያ መሐመድ በበኩላቸው፤ ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ አርሶ አደሮች ለልማት አመቺ የሆኑ መሬቶችን በበጋ ስንዴ እንዲያለሙ የተሰራው ስራ የአርሶ አደሩን ኑሮ እየቀየረ መሆኑን ተናግረዋል። ልማቱ እንደተጀመረ በሄክታር ይገኝ የነበረውን 25 ኩንታል ምርት በአሁኑ ወቅት ከእጥፍ በላይ ማድረስ ተችሏል ያሉት ወይዘሮ ሳሚያ፣ ለዚህ ስኬት የአርሶ አደሩ የግብዓት አጠቃቀም ማደግ እንዲሁም የግብርና ባለሙያዎች ቀጣይነት ያለው ድጋፍና ክትትል ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን ገልፀዋል። በተጨማሪም አርሶ አደሮች ከሚያመርቱት ምርት ተገቢውን ዋጋ ማግኘት እንዲችሉ ከዩኒየኖች ጋር የገበያ ትስስር መፈጠሩንና ዩኒየኖቹ ምርቱን ከአርሶ አደሩ መኖሪያ ቤት ድረስ ሄደው እንደሚረከቡ አስረድተዋል። የቦኬ ወረዳ አርሶ አደር የሆኑት ያህያ አደም በሰጡት አስተያየት፤ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህ በጀመሩት የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በየዓመቱ ከፍተኛ ምርት እያገኙ መሆኑን ገልፀዋል። ምርታቸውን ለገበያ በማቅረብም እስከ 300 ሺህ ብር ገቢ እያገኙ በመሆኑ ኑሯቸው መሻሻሉን አብራርተዋል። በጡሎ ወረዳ ኢፋ አንዶዴ ቀበሌ የሚኖሩት አርሶ አደር ጌታቸው አበበ በበኩላቸው፤ በየዓመቱ በበጋ መስኖ ልማት ግማሽ ሄክታር ማሳ እያለሙ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህም በየዓመቱ ከመቶ ሺህ ብር በላይ ገቢ በማግኘት ላይ መሆናቸውንና የተገኘውን ገቢ ለግብርና ግብዓት ግዢ እንዲሁም ደረጃውን የጠበቀ መኖሪያ ቤት ለመገንባት እንዳስቻላቸው ገልፀዋል።
በጋምቤላ ክልል በዘንድሮው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው ከ39 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ቀድመው በሚዘሩ ሰብሎች ተሸፍኗል
May 22, 2026 91
ጋምቤላ ፤ግንቦት 14/ 2018 (ኢዜአ) ፡-በጋምቤላ ክልል በዘንድሮው የመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው መሬት ውስጥ ከ39 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው ቀድመው በሚዘሩ ሰብሎችና የጓሮ አትክልቶች መሸፈኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ አቶ አንድሮው ቱት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በዘንድሮው የምርት ዘመን ከ180 ሺህ 850 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት፣ ከ5 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ግብ ተጥሎ እየተሰራ ይገኛል። በእስካሁኑ ሂደት በምርት ዘመኑ ለማልማት ታቅዶ ከነበረው መሬት ውስጥ ከ39 ሺህ 840 ሄክታር በላይ የሚሆነው ማሳ ቀድመው በሚዘሩ ሰብሎች መሸፈኑን ኃላፊው ገልጸዋል። ከእነዚህም መካከል በቆሎ፣ ሰሊጥ፣ ኦቾሎኒ፣ አኩሪ አተር እንዲሁም የተለያዩ የጓሮ አትክልቶች በዋናነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ተናግረዋል። በክልሉ ለማልማት ከታቀደው መሬት መካከል 99 ሺህ ሄክታሩ በሜካናይዜሽን ታግዞ ለማልማት እንዲቻል የእርሻ ትራክተሮች ስምሪት መደረጉንም አስታውቀዋል። ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግም ከ36 ሺህ ሄከታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም ለማልማት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በምርት ዘመኑ ለማልማት የታቀደው መሬት ሙሉ በሙሉ በዘር እንዲሸፈንና አንድም ማሳ ሳይታረስ እንዳይቀር የአመራርና የባለሙያዎች ስምሪት መደረጉን ኃላፊው ገልጸዋል። በዚህም ለአርሶና አርብቶ አደሮች የተጠናከረ የድጋፍና ክትትል ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን አስታውቀዋል። በክልሉ ሁሉም ወረዳዎች በልማት ፕሮጀክቶች በመታገዝ፤ የየአካባቢውን ስነ-ምህዳር መሰረት ያደረገ የበቆሎ፣ የማሽላና የሩዝ ምርጥ ዘር በበቂ ሁኔታ ቀርቦ መሰራጨቱንም አቶ አንድሮው ገልጸዋል። የአርሶና አርብቶ አደሩን ግንዛቤ በማጎልበት፣ የምርት ማሳደጊያ ግብዓቶችን በስፋት እንዲጠቀም በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም ኃላፊው ተናግረዋል። የኢታንግ ልዩ ወረዳ አርሶ አደር ጀምስ ቦት በሰጡት አስተያየት፤ በዘንድሮው የምርት ዘመን ከአራት ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የሦስት ሄክታር ብልጫ እንዳለውና የእርሻ መሬታቸውን ለማስፋት በትኩረት እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከስድስት ሄክታር በላይ ማሳ በበቆሎ፣ በማሽላና በሰሊጥ ሰብሎች ለማልማት በትኩረት እየሰሩ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የጎግ ወረዳ ነዋሪው ወጣት አርሶ አደር ኡሞድ ኡኮች ነው። በአሁኑ ወቅት ቀድሞ የሚዘራው የበቆሎ ሰብል የተወሰነ ማሳቸውን መሸፈኑን የገለጹት ወጣቱ አርሶ አደር፤ በቀጣይም ቀሪዎቹን የእርሻ መሬቶች በሌሎች ሰብሎች ለመሸፈን አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ግብርናና ቱሪዝም የሚያስገኙትን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማላቅ እየተከናወኑ ያሉ የምርምር ስራዎች ይጠናከራሉ
May 22, 2026 248
ጂንካ፤ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፡- ግብርናና ቱሪዝም የሚያስገኙትን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማላቅ እየተከናወኑ ያሉ የምርምር ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የጂንካ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ። በጂንካ ዩኒቨርስቲ ''ግብርናና ቱሪዝም ለአካታችና ለዘላቂ ልማት'' በሚል መሪ ሀሳብ ሁለተኛው አለም አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስ እየተካሄደ ነው። በዩኒቨርሲቲው እየተካሄደ ባለው ጉባኤ ተመራማሪዎች፣ የዩኒቨርስቲው ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎችና የማህበረሰብ ተወካዮች ታድመዋል። የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ዮሐንስ ይትባረክ (ዶ/ር) በምርምር ኮንፈረንሱ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፥ ግብርናና ቱሪዝም ለዘላቂ የልማትና የኢኮኖሚ እድገት ግብ ስኬታማነት የጀርባ አጥንት ናቸው ብለዋል። ጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ተልዕኮ ባሻገር ግብርናን እና ቱሪዝምን የምርምር እና የልህቀት ማዕከል ለማድረግና ዘርፎቹን ለማህበረሰብ ለውጥ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በዚህም ዩኒቨርሲቲው ችግር ፈቺ የጥናትና ምርምር ውጤቶችን በማፍለቅ ከቱሪዝም እና ከግብርናው ዘርፍ የሚገኘው ሀገራዊ ጥቅም እንዲጎለብት ሚናውን እየተወጣ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ኮንፈረንሱ ልምድና ተሞክሮን በመቀመር በዘርፉ የተሻለ ለውጥ ለማምጣት እንደሚያግዝም አመልክተዋል። በመድረኩ የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ አለማየሁ ባውዲ በበኩላቸው ሀገራችን ቀጣይነት ያለው ኢኮኖሚ በመገንባት የዜጎችን ህይወት ለመለወጥ እየሰራች መሆኑን አንስተዋል። ይህንን ሀገራዊ ራዕይ እና ተልዕኮ ለማሳካት ችግር ፈቺና መፍትሔ አመላካች የምርምር ውጤቶች እና ተጨባጭ ማሳያዎች ያስፈልጋሉ ብለዋል። ዩኒቨርሲቲዎች እና የምርምር ተቋማትም በተለይ በቱሪዝምና በግብርናው መስክ የምርምር ውጤቶችን በማፍለቅ ለተያዘው ዘላቂ ልማትና እድገት ግብ መሳካት ሚናቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል። በመድረኩ የተጋበዙት የብሪቲሽ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ የሶሻል አንትሮፖሎጂ ተመራማሪ ሻውና ሎቶስኪ (ዶ/ር)፥ ከ23 ዓመታት በፊት ኢትዮጵያን በቅርበት እንደሚያውቋት አንስተዋል። በሙርሲ ባህል እና አኗኗር ላይ ጥናቶችን ያከናወኑት ተመራማሪዋ፥ አካባቢው ዕምቅ የቱሪዝም ሀብት ያለበት እንደሆነም አመልክተዋል። በአካባቢው የጂንካ ዩኒቨርሲቲ መቋቋሙ ደግሞ እነዚህን እምቅ ሀብቶች በማልማት ጥቅም ላይ ለማዋል ያግዛል ነው ያሉት። የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብረሃም አታ በበኩላቸው የጂንካ ዩኒቨርሲቲ ከመማር ማስተማር ስራው ባሻገር ለዞኑ ማህበረሰብ ለውጥ በምርምር የተደገፉ የመፍትሔ ሀሳቦችን በማፍለቅ ከፍተኛ እገዛ እያደረገ ነው ብለዋል። አካባቢው እምቅ የግብርናና የቱሪዝም ሀብት ያለበት በመሆኑ ይህንን ሀብት በማልማት ጥቅም ላይ ለማዋል እንዲቻል ዩኒቨርሲቲው ሙያዊ ድጋፉን እንዲያጠናክር ጠይቀዋል፡፡ በምርምር ኮንፍረንሱ ላይም አለም አቀፍ፣ አህጉራዊ፣ ሀገራዊ እና አካባቢያዊ ተሞክሮዎችን የሚያስቃኙ የጥናት ውጤቶች ይቀርባሉ።
ሁለገብ የገበያ ማዕከሉ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ አስችሎናል-ሸማቾች
May 22, 2026 78
አዲስ አበባ፤ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ሁለገብ የገበያ ማዕከሉ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ምርቶችን በብዛት፣ በጥራትና በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ማስቻሉን ሸማቾች ገለጹ። በአዲስ አበባ የተገነቡ ሁለገብ የገበያ ማዕከላት የግብይት ሰንሰለቱን በማሳጠርና የዋጋ ንረትን በመቀነስ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛሉ። ኢዜአ በለሚ ኩራ የገበያ ማዕከል ባደረገው ቅኝት ሸማቾች በማዕከላቱ ሁሉንም ዓይነት ምርቶች በማግኘት ከእንግልት መዳናቸውን ገልጸዋል። በማዕከሉ የሚገኙ የምርቶች ዋጋም ከማዕከላቱ ውጭ ከሚገኙ ገበያዎች አንጻር ሰፊ ልዩነት ያለውና ሸማቹ በተመጣጣኝ ዋጋ መግዛት የሚያስችለው መሆኑን ተናግረዋል። በለሚ ኩራ የገበያ ማዕከል ሲገበያዩ ያገኘናቸው አቶ አሊ እንድሪስ፤ የማዕከሉ መገንባት ጥራታቸውን የጠበቁ የሰብል ምርቶች፣ አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ ሌሎች ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ማስቻሉን ገልጸዋል። ሁሉንም ዓይነት የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች በአንድ ማዕከል ማግኘታቸው የገበያ አማራጭ እንደፈጠረላቸውም ገልጸዋል። የግብርና ምርቶችን በአቅራቢያችን በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመት የምንችልባቸው የገበያ ማዕከላት ወደ አገልግሎት መግባታቸው ተጠቃሚ እንድንሆን አስችሎናል ያሉት አቶ ባይሳ ግርማ ናቸው። በተጨማሪም የአትክልትና የፍራፍሬ ምርቶች በየቀኑ የሚገቡ ጥራት ያላቸው በመሆናቸው ለጤና ጠቃሚ መሆናቸውን ይናገራሉ። በገበያ ማዕከሉ ጤፍን ጨምሮ የተለያዩ የግብርና ምርቶች አቅማቸውን ባገናዘበ መልኩ ማግኘታቸውን ጠቅሰው ከውጭ ገበያ ጋር ሰፊ ልዩነት እንዳለው የገለጹት ደግሞ አቶ ክብሮም ገብረእግዚአብሔር ናቸው፡፡ በመዲናዋ አራቱም ማዕዘናት የተገነቡት የገበያ ማዕከላት ከደላላ ጣልቃ ገብነት ነጻ የሆኑና የግብይት ሰንሰለቱን በማሳጠር አምራቾች ምርቶቻቸውን በቀጥታ ለተጠቃሚው እንዲያቀርቡ በማስቻል ላይ ይገኛሉ። በለሚ ኩራ የገበያ ማዕከል ያነጋገርናቸው አምራች አብርሃም ንጉሴ እንዳሉትም፤ መንግስት የመስሪያ ቦታውን በነጻ በመስጠት ላደረገላቸው ትልቅ ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። በዚህም ጥራት ያላቸውን የግብርና እና የአትክልት ምርቶች ከውጪው የገበያ ዋጋ ከ15 እስከ 20 በመቶ በሚደርስ ቅናሽ ለህብረተሰቡ እያቀረቡ መሆኑን አረጋግጠዋል። ወይዘሮ መሰረት አቦባሬ እና አቶ ቶልቻ ንጉሴ በበኩላቸው፤ ምርቶቹ ያለ ምንም ጣልቃ ገብነት የሚቀርቡ በመሆናቸው የገበያ ንረትን ለመቆጣጠር ትልቅ አቅም መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህም ህብረተሰቡን በተመጣጣኝ ዋጋ በማገልገል ገበያውን ለማረጋጋት ያስቻለ በመሆኑ፣ ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ የከተማዋ ነዋሪዎችም በማዕከላቱ በደስታ እየተገበያዩ ይገኛሉ ብለዋል።
በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መጥቷል
May 22, 2026 213
አዲስ አበባ፤ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መምጣቱን በተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) ገለጹ። በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ኢትዮጵያን ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት መዳረሻ ማድረጉንም ገልጸዋል። በኢትዮጵያ እና ዱባይ መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ 6 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱም ተገልጿል። በዱባይ የንግድ ምክር ቤት የተዘጋጀው የዱባይ - ኢትዮጵያ ቢዝነስ ትብብር ፎረም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። በተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የንግድና ኢንቨስትመንት የስበት ማዕከል ናት። ኢትዮጵያ በቀጣናው ለኢንቨስትመንት የተመቸ ስነ ምህዳር፣ የጂኦግራፊ አቀማመጥ ለስራ ብቁ የሆነ የሰው ሀይል ያላት ምቹ የቢዝነስ መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የወጣቶች ምድር የአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን አፍሪካውያን የገበያ መግቢያ በርና የምቹ የኢንቨስትመንት መዳረሻ መሆኗንም ገልጸዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ሁሉንም የንግድና ኢንቨስትመንት እንቅፋቶችን በማስወገድ ኢትዮጵያን ለንግድና ኢንቨስትመንት የተመቸች ሀገር አድርጓታል ብለዋል። የመስኮት የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ጨምሮ በተሟላ መሰረተ ልማት ፈጣንና ቀልጣፋ የንግድ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ሥርዓት ተዘርግቷል ብለዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ግዙፉ የአየር መንገድ፣ የባቡርና ተሽከርካሪ የተሳለጠ የሎጂስቲክስ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሰረተ ልማት መዘርጋቷን ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መሆኑን ገልጸው፣ የሁለቱ ሀገራት መሪዎች በፅኑ መሰረት ላይ እንዲገነባ አድርገውታል ብለዋል። የዱባይ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዝዳንትና ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሞሐመድ አሊ ራሸድ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ወሳኝ የንግድ ኢንቨስትመንትና የገበያ መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ወሳኝ ስትራቴጂካዊ መልክዓምድር ላይ የምትገኝ በአፍሪካ ግንባር ቀደም የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ እንደምትገኝም ተናግረዋል። የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች እና ኢትዮጵያ ያላቸው የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ እያደገ መምጣቱንም ጠቅሰዋል። ሁለቱ ሀገራት በንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ግብርናና መሰል መስኮች ትብብራቸው እያደገ በመምጣቱ የተባበሩት ዐረብ ኢምሬት የኢትዮጵያ ካምፓኒዎች መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። በዱባይ ከአንድ ሺህ 660 በላይ የኢትዮጵያ ኩባንያዎች በንግድ፣ ሪልስቴት፣ ሎጂስቲክስና መሰል ዘርፎች ተሰማርተው እንደሚገኙ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ እና ዱባይ መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ 6 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱን ገልጸው፤ የዛሬው ፎረምም የሁለቱን ሀገራት ኩባንያዎች ንግድና ኢንቨስትመንት ያጠናክራል ብለዋል።
የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ መንገድ ፕሮጀክት በይፋ ተመርቆ ለአገልግሎት በቃ
May 22, 2026 162
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ ከ672 ሚሊየን ብር በሚበልጥ ወጪ የተገነባው የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ መንገድ ፕሮጀክት በይፋ ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል። በምረቃው ላይ የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፋ መሀመድ ፣ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ ፣የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር አቶ መሀመድ አብዱራህማን ፣የክልሉ የመንገዶች ቢሮ ሀላፊ አቶ ኢድሪስ ሙሴ እና ሌሎችም ተገኝተዋል። የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፋ መሀመድ በዚህ ወቅት እንደገለጹት ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ መንገድ ፕሮጀክት የከተማውን የንግድ ፣ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴን ለማሳለጥ ያስችላል። መንገዱ ህብረተሰቡን ጥራት ያለው የመንገድ መሰረተ ልማት ተጠቃሚ ከማድረጉም ባሻገር የከተማውን ገፅታ በመለወጥ ረገድ የጎላ ጠቀሜታ እንደሚያበረክትም ገልጸዋል። በክልሉ ከለውጡ ወዲህ የተከናወኑ ሁለተናዊ የልማት ስራዎችን በእጥፍ በማሳደግ የህዝቡን የልማት ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማጠናከር በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ በበኩላቸው የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ የመንገድ ፕሮጀክት የጅግጅጋ ከተማን ልማትና ዕድገት በማፋጠን በኩል ያለው ጠቀሜታ ከፍ ያለ ነው ብለዋል። ሚኒስትሯ የመንገድ ፕሮጀክቱ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ድረስ ከፍተኛ አስተዋኦ ላበረከቱ ተቋማት እና ለክልሉ መንግስት ከፍተኛ ምስጋና አቅርበዋል። የኢትዮጵያ የመንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር አቶ መሀመድ አብዱራህማን አስተዳደሩ ሀገራዊ የመንገድ መሰረተ ልማት ዕቅድን ለማሳካት እየሰራ መሆኑን ጠቁመው የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ የመንገድ ፕሮጀክትም የዚሁ አካል ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ተግባራዊ የተደረገው የመንገድ ፕሮጀክቱ በይርጋለም የመንገድ ኮንስትራክሽን ድርጅት አማካኝነት የተገነባ መሆኑንም ተገልጿል። የመንገድ ፕሮጀክቱ 7 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ሲሆን 30 ሜትር ስፋት ያለውም መሆኑን የክልሉ መገናኛ ብዙሃን ኤጀንሲ ዘገባ ያሳያል ።