ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በነቀምቴ ከተማ ህብረተሰቡ ለሰላምና ልማት መጠናከር ባሳየው ቁርጠኝነት ስኬታማ ሥራዎች ተከናውነዋል
Jun 23, 2026 529
ነቀምቴ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በነቀምቴ ከተማ ህብረተሰቡ ለሰላምና ልማት መጠናከር ባሳየው ቁርጠኝነት በርካታ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውን የኦሮሚያ ክልል ፀጥታ እና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ ገለጹ። በነቀምቴ ከተማ በ189 ሚሊየን ብር ወጪ የተገነቡ ሼዶች ዛሬ ተመርቀዋል። በሼዶቹ ምረቃ ላይ የኦሮሚያ ክልል ፀጥታ እና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ፣ የክልሉ ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሀብት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ኮከቤ ዲዳ፣ የነቀምቴ ከተማ ከንቲባ መሰረት ሀይሉ እና ሌሎች የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ የከተማውንና አካባቢውን ሰላም ለማጠናከር ህብረተሰቡን ከፀጥታ አካላት ጋር በማስተባበር በተሰራው ሥራ የአካባቢው ሰላም ማጠናከርና የልማት ሥራዎችን በስፋት ማከናወን መቻሉን ተናግረዋል። በተለይ ለከተማው ወጣቶች የሥራ አማራጭ እየተመቻቸ መሆኑን ጠቅሰው፤ ወጣቶችም የሥራ ዕድሉን በአግባቡ በመጠቀም ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች መትረፍ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የነቀምቴ ከተማ ከንቲባ መሰረት ሀይሉ በበኩላቸው በከተማዋ ሰፊ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን ገልፀዋል። ማህበረሰቡ ለሰላሙ ዘብ ቆሞ ለልማት ባሳየው ቁርጠኝነት የተጀመሩ የልማት ሥራዎች በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ ተጠናቀው ለአገልግሎት እየበቁ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት በበቁት ሼዶችም ወጣቶች ሰርተው ራሳቸውን እንዲለውጡ ለማስቻል የከተማዋ አስተዳደሩ የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል። የነቀምቴ ከተማ አስተዳደር ማዘጋጃ ቤት ኃላፊ አቶ ቶለሳ ደጋጎ ዛሬ ለምረቃ የበቁት ሼዶች በመንግሥት 189 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገባቸው መሆኑን ተናግረዋል። ሼዶቹም በ104 ማህበራት ለተደራጁ 520 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር የሚያስችሉ መሆኑን ገልጸው፤ ወጣቶቹም በከብት ማድለብ፣ በሥጋና እንቁላል ዶሮ እርባታ፣ በወተት ልማትና በመሰል የሥራ ዘርፎች የተደራጁ ናቸው ብለዋል። የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ወጣቶች መካከል ወጣት ሙሉጌታ መልካሙ ከጓደኞቹ ጋር በወተት ምርት በመደራጀት በአምስት ሚሊየን ብር ካፒታል ሥራ ለመጀመር መዘጋጀታቸውንም ተናግሯል። የከተማ አስተዳደሩ ያመቻቸላቸውን እድል በመጠቀም ሰርተው ራሳቸውን ለመለወጥ ማቀዳቸውን ተናግሯል። ሌላኛው የሥራ እድል ተጠቃሚ ወጣት ቢቂላ ለማ በበኩሉ ከብት በማድለብ ሥራ ላይ ለመሰማራት እንደተደራጁ ገልጾ፤ በስራቸው ውጤታማ ለመሆን ተግተው እንደሚሰሩ አመልክቷል። መንግስት ያመቻቸውን የሥራ እድል በመጠቀም ሰርቶ ለመለወጥ ቁርጠኛ መሆኑንም አረጋግጧል።
መንግሥት በመደመር እሳቤ ዘመን ተሻጋሪና ሜጋ መሠረተ ልማቶችን እውን አድርጓል-ብሩክ ታዬ(ዶ/ር)
Jun 23, 2026 550
አዲስ አበባ፤ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦የለውጡ መንግሥት በመደመር እሳቤ ውጤታማ የፋይናንስ ሥርዓትን በመከተል ለትውልድ የሚሻገሩ ሜጋ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶችን እውን ማድረጉን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት "ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር" በሚል መሪ ሀሳብ "ኢትዮጵያ ታከናውናለች" ጉባኤ በሳይንስ ሙዚየም ተካሂዷል። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሩክ ታዬ (ዶ/ር) በሰጡት ማብራሪያ፥ የኢትዮጵያ የመሠረተ-ልማት ጉዞ ለዘመናት ከዘለቀው ሀገራዊ ትልም ተነሥቶ፣ አሁን ላይ በትጉህና ግልጽ መርሆዎች እንዲሁም በተቀናጀ አፈጻጸም ወደሚመራ የለውጥ ዘመን መሸጋገሩን ገልጸዋል። ለዚህ ስኬት ደግሞ የለውጡ መንግሥት ሀገራዊ ተስፋን ከተቋማዊ አቅም ጋር ወደሚያጣጥም፣ ይበልጥ አመቺ፣ ቅደም ተከተላዊ እና የፋይናንስ ሥርዓትን ወደ ተከተለ አካሄድ ቁርጠኛ ሽግግር በማድረጉ የተመዘገበ ነው ብለዋል። የእያንዳንዱ ውጤት መሠረትም የለውጡ መንግስት የተከተለው የመደመር እሳቤ መሆኑን አስረድተዋል። ይህ የመደመር እሳቤ አካሄድም መሠረተ ልማትን ወደ ቀጣይነት ያለው ሀገራዊ እሴት እና ለትውልድ ተሻጋሪ ሀብት እንዲቀየር እያደረገው እንደሚገኝ ዋና ሥራ አስፈጻሚው አስታውቀዋል። በተጨማሪም የታዳሽ ሃይል፣ የዲጂታል ማስፋፊያ፣ የትራንስፖርት፣ የኮንስትራክሽን እና የአረንጓዴ ቴክኖሎጂ ስትራቴጂካዊ ዘርፎች ሀገሪቱ የምታደርገውን የለውጥና የብልጽግና ጉዞ እየመሩት እንደሚገኙም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በራሷ አቅም ፈጣን እድገቷን ለማስቀጠል እየተጋች እንደምትገኝ በማብራሪያቸው ላይ አመላክተዋል። በዚህም በርካታ ግዙፍ መሠረተ ልማቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት እየተደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል። መንግስት መሠረተ-ልማትን በተመለከተ ውጤታማ የሆኑ አሠራሮችን በቀጣይነት በመተግበሩ አመርቂ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ የምግብ ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ የሚያስችል ፈጣን ሽግግር ላይ ትገኛለች
Jun 23, 2026 522
አዲስ አበባ፤ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ በምግብ ራስን የመቻል ግብን ለማሳካትና የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚያስችል ፈጣን የምርታማነት ሽግግር ላይ እንደምትገኝ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስትቲዩት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ሀሳብ የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ በሳይንስ ሙዚየም ተካሂዷል። የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በጉባኤው ላይ የግብርና ዘርፍ የለውጥ ጉዞን በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም ኢትዮጵያ በዘርፉ ስትራቴጂካዊ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ፣ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ጉልህ ማሻሻያዎችን ማከናወኗን ጠቅሰዋል። በዚህም የሀገሪቱን የግብርና ዘርፍ ከነበረበት ከእጅ ወደ አፍ ልምምድ በማላቀቅ አሁን ላይ ከእርሻ ወደ ንግድ እና የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ወደሚያስችል ጠንካራ መሠረት እየተሸጋገረ ነው ብለዋል። ለዚህም ከ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ ጋር የተጣጣሙ ስትራቴጂዎችንና የፖሊሲ ማዕቀፎችን በመንደፍ፤ የመንግሥት፣ የግል ዘርፉንና የህዝብ አጋርነትን ለማጠናከር፣ ፈጠራንና የግብርና ቢዝነስን ለማስፋፋት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የግብርናው ዘርፍ ይበልጥ ምርታማ፣ በገበያ መር እና ለተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ ተፅዕኖዎች የማይበገር የምርታማነት ሥርዓት እየተገነባ መሆኑን ገልጸዋል። ቀደም ሲል ከውጪ በሚገቡ ምርቶች ላይ ጥገኛ የነበረችው ኢትዮጵያ አሁን ላይ በሀገር ውስጥ ተኪ ምርቶችን በማስፋት ተጨባጭ ውጤቶች በማምጣት ታሪኳን እየቀየረች ነው ብለዋል። በስንዴ ምርት ራሷን ከመቻል አልፋ በአፍሪካ ቀዳሚዋ አምራች ሀገር መሆኗንም ተናግረዋል። የሌማት ትሩፋትና መሰል በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያሳተፉ ሀገር በቀል ተነሳሽነቶችን በማዳበር፣ ቴክኖሎጂንና የሰው ሰራሽ አስተውሎትን በመጠቀም የግብርና ምርታማነት እያደገ መሆኑን ጠቅሰዋል። በግብርናው ዘርፍ የተወሰዱ ስትራቴጂካዊ እርምጃዎች ለዘላቂ የግብርና ልማት፣ ለገጠር ብልጽግና እና ለጠንካራ ኢኮኖሚ መሰረት መጣላቸውን ገልጸዋል። ይህም ኢትዮጵያ ወደፊት እየተራመደችና ተጨባጭ ለውጥ እያስመዘገበች መሆኑን በተግባር እንደሚያሳይ አመልክተዋል። የግብርናው ዘርፍ ማሻሻያ የዘርፉን አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት ድርሻ ማሳደጉን ተናግረዋል።
ባለፉት ስምንት ዓመታት በውጭ ዕዳ ጫና ቅነሳ፣ በውጭ ምንዛሬ አስተዳደርና በዋጋ ንረት ቅነሳ ትርጉም ያለው ውጤት ተመዝግቧል
Jun 23, 2026 468
አዲስ አበባ፤ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በውጭ ዕዳ ጫና ቅነሳ፣ በውጭ ምንዛሬ አስተዳደርና በዋጋ ንረት ቅነሳ ትርጉም ያለው ውጤት ማምጣቱን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ገዥ እየብ ተካልኝ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ሀሳብ የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ በሳይንስ ሙዚየም ተካሂዷል። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ገዥ እየብ ተካልኝ (ዶ/ር) ባለፉት ስምንት ዓመታት በሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በተወሰዱ እርምጃዎች የተገኙ ውጤቶች ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያ በግብርና፣ ማዕድን፣ ኢንዱስትሪ፣ ቱሪዝምና ዲጂታል መስኮች ተጨባጭ ውጤቶች እንዲመዘገብ ማስቻሉን አንስተዋል። ከለውጡ በፊት የውጭ ዕዳ ጫና ከፍተኛ እንደነበር አስታውሰው፤ የውጭ ምንዛሬ እጥረት እንዲሁም ከመደበኛው የዶላር ምንዛሬ የጥቁር ገበያው ምንዛሬ በከፍተኛ ደረጃ መብለጡ ትልቅ ችግር እንደነበር አንስተዋል። ሪፎርሙ የዕዳን ጫናን ለመቀነስ ከማስቻሉም ባሻገር የውጭ ምንዛሬ እጥረት ችግሮች እንዲቀረፉ ማድረጉን አመልክተዋል። የዋጋ ንረትን በመቆጣጠር፣ የውጭ ምንዛሬን ገበያ መር በማድረግ፣ የገንዘብና የፊስካል ፖሊሲን በማዘመን ትርጉም ያለው ውጤት ተገኝቷል ብለዋል። በዚህም የፋይናንስ ዘርፉን የሚያጠናክሩ ተግባራት ተከናውነዋል ያሉት ገዥው ለዘላቂና አካታች ዕድገት ጠንካራ መሠረት ተጥሏል ብለዋል። በኢትዮጵያ የዋጋ ግሽበቱ እስከ 34 በመቶ የደረሰበት ጊዜ እንደነበር ያስታወሱት እዮብ (ዶ/ር) በተወሰደው የማሻሻያ እርምጃ የዋጋ ግሽበቱን ወደ ነጠላ አሃዝ ማውረድ መቻሉን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የውጭ ንግድ ገቢ እያደገ መምጣቱን ገልጸው ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላቸው ተወዳዳሪነት እየጨመረ ነው ብለዋል። ይህም የተወሰደው የማሻሻያ ውጤት መሆኑንም በማብራሪያቸው አመልክተዋል።
በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ በሁሉም ዘርፍ ለትውልድ የሚሻገር የላቀ ዕድገት እያስመዘገበ ነው
Jun 23, 2026 391
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ በሁሉም ዘርፍ ለትውልድ የሚሻገር የላቀ ዕድገት እያስመዘገበ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ሀሳብ የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ በአዲስ አበባ ሳይንስ ሙዚየም ተካሂዷል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ ሉዓላዊነቷን ለዘመናት ጠብቃ የቆየች የጥንታዊ ሥልጣኔ ባለቤት ሀገር ናት። በ21ኛው ክፍለ ዘመንም ሕዝቦቿን በማስተባበር ያለማንም ድጋፍ ታላቁን የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በዓባይ ወንዝ ላይ የገነባች የልማት ተምሳሌት መሆኗን አውስተዋል። በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም ዕድገትን ከማፋጠን ባሻገር ለመጪው ትውልድ የበለጸገች ኢትዮጵያን ለማስተላለፍ በተከናወኑ ተግባራት ዘርፈ ብዙ ስኬት እየተገኘ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ዕድገት በአዲስ የስኬት ምዕራፍ እየተጓዘ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለአብነትም ከ30 በመቶ በላይ ደርሶ የነበረውን የዋጋ ንረት ወደ ነጠላ አሃዝ ማውረድ መቻሉን አስረድተዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም የውጭ ንግድ ተወዳዳሪነት አቅምን በማሳደግ ጭምር ኢትዮጵያ የ10 ነጥብ 2 በመቶ የአፍሪካን ፈጣን ዕድገት እንደምታስመዘግብ አስረድተዋል። እነዚህ ውጤቶች በአጋጣሚ ያልተገኙና የዜጎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ናቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በጥንቃቄ ተግባራዊ የተደረገው ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ትግበራ ውጤት መሆናቸውን ነው ያብራሩት። በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር ትግበራም በመደመር መርህ ዕድገትን የሚያሳልጡ የአሠራር ሥርዓቶች ተግባራዊ መሆናቸውን አብራርተዋል። መደመር የአብሮነት እውነተኛ ትርጉም ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ መደመር ዕድገት የሚጠናከረው የተለያዩ ጥረቶች እርስ በርስ ሲደጋገፉ መሆኑን ያምናል ብለዋል። የኢትዮጵያ የብዝሃ ኢኮኖሚ ዕድገት እመርታን ለማስቀጠል በከፍተኛ ትጋት እየተሰራ እንደሚገኝም አስረድተዋል። የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የለውጥ ጉዞ የሚያሳልጥ ትብብርና አጋርነት አስፈላጊ መሆኑን አስረድተዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያ የማንሠራራት ጉዞ በማጽናት የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማስቀጠል የተሻለች ሀገርን ለትውልድ የማሻገር ጉዞ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።
ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ከተረጂነት ለመላቀቅ የተያዘውን ዕቅድ የሚያሳኩ ናቸው
Jun 23, 2026 168
አሶሳ፤ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ከተረጂነት ለመላቀቅ የተያዘውን ዕቅድ የሚያሳኩ ናቸው ሲሉ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ። የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች በተረጂነት ቅነሳና በምግብ ሉዓላዊነት ዙሪያ በተዘጋጀ የ5 ወራት ዕቅድ ላይ ውይይት አድርገዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በውይይቱ ወቅትም እንደተናገሩት፤ ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ከተረጂነት ለመላቀቅ የተያዘውን ዕቅድ የሚያሳኩ ናቸው። በክልሉ በቅርብ ዓመታት የተጀመረው ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም የመሸፈን ትግበራ አበረታች ውጤት የታየበትና የስራ ባህልን የቀየረ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በቂ ምርትን በመያዝ አደጋን የመቋቋም አቅምን ለማሳደግ እና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎችን አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሐመድ አብዱላዚዝ በበኩላቸው፤ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመሸፈን በሚደረገው ጥረት በግብርናው ዘርፍ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል። በዚህም በክልሉ የተለያዩ የግብርና ውጤቶችን በማምረት ለአደጋ ጊዜ ምላሽ ለመስጠት ዝግጅት መደረጉንም አክለዋል።
ከተማዋ ያሏትን ፀጋዎች በአግባቡ በማልማት ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ
Jun 23, 2026 200
አርባ ምንጭ፤ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ አርባምንጭ ከተማ ያሏትን ፀጋዎች በአግባቡ በማልማት ማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የከተማዋ አስተዳደር አስታወቀ። መንግስት የከተሞችን ገጽታ በመለወጥ ለነዋሪዎች ምቹ ከማድረግ ባለፈ የዜጎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ እንዲሆኑ በትኩረት እየሰራ ይገኛል። በዚህም በሀገሪቱ በሚገኙ ከተሞች በስፋት እየተከናወኑ የሚገኙ የኮሪደር፣ የወንዝና የሀይቅ ዳርቻ የልማት ስራዎች ገፅታን ከመቀየር ያለፈ ግብን ይዘው እየተከናወኑ ነው። ይህም ከተሞቹን ለኑሮ፣ ለስራ፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ በማድረግ ፈጣን ዕድገት እንዲያስመዘግቡ እያገዘ ሲሆን የአርባ ምንጭ ከተማም በልማት ስራዎቹ በፈጣን ዕድገት ውስጥ ከሚገኙ ከተሞች አንዷ እየሆነች ነው። የከተማዋ አስተዳደር ከንቲባ መስፍን መንዛ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ከተማዋ ያሏትን ፀጋዎች በአግባቡ በማልማት ማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ። የለውጡ መንግስት ከተሞችን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ በዘረጋው ትልም የከተማዋ ፀጋዎች ተገልጠው ወደ ሀብት እየተቀየሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የእግረኞች፣ የብስክሌት፣ የአረንጓዴ ልማት፣ የህዝብ መዝናኛ፣ የስፖርት ማዘውተሪያዎችን ያካተተ 20 ኪሎ ሜትር የተቀናጀ የኮሪደር ልማት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ከእነዚህም በተለየ ስያሜ እየተገነቡ ያሉ የደረጃ መንገዶችን ጨምሮ የኩልፎ ወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎች የከተማዋን ፈጣን ዕድገት ማሳያዎች ናቸው ብለዋል። በከተማው በመንግስትና በህዝቡ ተሳትፎ የተገነቡ የህክምና ተቋማትና ደረጃውን የጠበቀ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል መኖሩን ጠቅሰው የከተማዋን ዕድገት ለማፋጠን እየተከናወኑ የሚገኙ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። የከተማዋ ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ እየተከናወኑ የሚገኙ አዳዲስ የልማት ፕሮጀክቶች የከተማዋን ዕድገት እያፋጠኑ መሆኑን መስክረዋል። አቶ ሙሴ ጉማራ የተባሉ የከተማዋ ነዋሪ እንደገለፁት፤ በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉት የኮሪደር፣ የወንዝ ዳርቻና የስታዲየም ግንባታዎችና ሌሎች መሰረተ ልማቶች በከተማዋ ፈጣን ዕድገት እንዲመጣ እያደረጉ ነው ብለዋል። የመንገድ እና የመብራት መሠረተ ልማቶች እንዲሁም የቤቶች፣ የጤና እና የትምህርት ተቋማት ዘመኑን በሚመጥን መልኩ በመገንባታቸው የከተማዋ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት እየተረጋገጠ ይገኛል ብለዋል።
በካፋ ዞን የሚገኙ ሀብቶችን በማልማትና በማስተዋወቅ የዘርፉን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
Jun 23, 2026 180
ቦንጋ ፤ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በካፋ ዞን የሚገኙ ባህላዊ፣ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ ሀብቶችን በማልማትና በማስተዋወቅ የዘርፉን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት መደረጉን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። የካፋ ዘመን መለወጫ በዓል (ማሽቃሮ) በአለም ቅርስነት እንዲመዘገብ በባህልና ስፖርት ሚኒስቴር የተጠና ጥናት የመጀመሪያ ዙር የባለድርሻ አካላት የውይይት መድረክ በቦንጋ ከተማ ተካሄዷል። በመድረኩ መልዕክት ያስተላለፉት የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ፤ የካፋ ሕዝብ የበርካታ ባሕላዊ፣ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ ሀብቶች ባለቤት መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ከነዚህም የዘመን መለወጫ በዓል "ማሽቃሮ" አንዱ መሆኑን ጠቁመው በተገቢው ጥናት ተደግፎና ለምቶ በአለም ቅርስነት እንዲመዘገብ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። ዞኑ በርካታ የባህል፣ የታሪክ፣ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የቱሪዝም ሃብት መገኛ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የካፋ ዞን ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ ታሪኳ ታከለ ናቸው። የካፋ ዘመን መለወጫ በዓል "ማሽቃሮ"ን በማስተዋወቅ በዩኔስኮ የማይዳሰስ ቅርስ ሆኖ እንዲመዘገብ በየደረጃው ሲቀርቡ የነበሩ ጥያቄዎችን በመቀበል የባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ጥናት ሲያካሄድ ቆይቶ ለውይይት ማቅረቡን ገልፀዋል። የጥናት ፅሁፉን ለመድረኩ ያቀረቡት በሚኒስቴሩ የባህል እሴቶች ጥናትና ልማት ባለሙያው አቶ ማህተቤ ጥላሁን፤ ሚኒስቴሩ የሕዝቦችን ባህላዊና ታሪካዊ እሴቶች በማጥናት፣ በመሰነድና በማስተዋወቅ በዓለም የማይዳሰስ ቅርስነት እንዲመዘገብ በሰፊው እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም የካፋ ዘመን መለወጫ በዓል "ማሽቃሮ" የባህል መዳረሻ ሆኖ እንዲተዋወቅና በአለም ቅርስነት እንዲመዘገብ ሲደረግ የነበረውን ጥናት በማጠናቀቅ የመጀመሪያ ዙር ውይይት ተደርጎ ለቀጣይ ስራ የሚጠቅም ግብዓት መገኘቱን ተናግረዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል የካፋ ባህል ልማት አማካሪ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ብርሃኑ ሀይሌ ፤ ማሽቃሮ በካፋ ህዝብ ዘንድ ለበርካታ ዘመናት ያለልዩነት የሚከበር አንድነትን፣ ሰላምንና ፍቅርን የሚያጠናክር በዓል መሆኑን ገልፀዋል። በዓሉ ካለው ባህላዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ አንፃር ከአካባቢው አልፎ በሀገርና በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲታወቅ፣ ይበልጥ እንዲለማና የባህል መዳረሻ ሆኖ በቀጣይነት ለትውልድ እንዲተላለፍ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል ብለዋል፡፡
የኢትዮጵያ የመሠረተ-ልማት ጉዞ በትጉህና ግልጽ መርሆዎች እና በተዋቀረ አፈጻጸም ወደሚመራ የለውጥ ዘመን ተሸጋግሯል
Jun 23, 2026 235
አዲስ አበባ፤ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የመሠረተ-ልማት ጉዞ ለዘመናት ከዘለቀው ሀገራዊ ትልም ተነሥቶ አሁን ላይ በትጉህና ግልጽ መርሆዎች እንዲሁም በተዋቀረ አፈጻጸም ወደሚመራ የለውጥ ዘመን መሸጋገሩን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ብሩክ ታዬ ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ቃል የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ በመካሄድ ላይ ነው። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ብሩክ ታዬ በሰጡት ማብራሪያ፣ የኢትዮጵያ የመሠረተ-ልማት ጉዞ ለዘመናት ከዘለቀው ሀገራዊ ትልም ተነሥቶ አሁን ላይ በትጉህና ግልጽ መርሆዎች እንዲሁም በተዋቀረ አፈጻጸም ወደሚመራ የለውጥ ዘመን ተሸጋግሯል ብለዋል፡፡ ለዚህ ስኬት ደግሞ የለውጡ መንግሥት ሀገራዊ ተስፋን ከተቋማዊ አቅም ጋር ወደሚያጣጥም፣ ይበልጥ አመቺ፣ ቅደም ተከተላዊ እና የፋይናንስ ሥነ-ሥርዓትን ወደ ተከተለ አካሄድ ቁርጠኛ ሽግግር ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይህም መሠረተ ልማትን ወደ ቀጣይነት ያለው ሀገራዊ እሴት እና ለትውልድ ተሻጋሪ ሀብት እንዲቀየር እያደረገው ይገኛል ነው ያሉት። የንጹሕ ኢነርጂ፣ የዲጂታል ማስፋፊያ፣ የትራንስፖርት፣ የኮንስትራክሽን እና የአረንጓዴ ቴክኖሎጂ ስትራቴጂካዊ ዘርፎች ሀገሪቱ የምታደርገውን የለውጥና የብልጽግና ጉዞ እየመሩት መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ ኢትዮጵያ ዕድገቷ ራሱን ችሎ የሚቀጥልና ለውጥ የሚያመጣበት ደረጃ ላይ ለመድረስ በትጋት እየገነባች ትገኛለች ብለዋል፡፡
የመስኖ ፕሮጀክቱ የአካባቢውን አርሶ አደር ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ዓመቱን ሙሉ ለማምረት አስቻይ ሁኔታን ይፈጥራል
Jun 23, 2026 157
መተማ፤ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ በምእራብ ጎንደር ዞን በመተማ ወረዳ በኩመር አፍጥጥ ቀበሌ ግንባታው የተጀመረው የመስኖ ፕሮጀክት የአካባቢውን አርሶ አደር ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ዓመቱን ሙሉ ለማምረት አስቻይ ሁኔታን እንደሚፈጥር የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በዞኑ የአካባቢውን ማህበረሰብ ዘላቂ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል የመስኖ ፕሮጀክት ማስጀመሪያ ስነ ስርዓት ዛሬ ተካሄዷል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይም የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አንዳርጌ ጌጡ እንደገለጹት፤ የመስኖ ፕሮጀክቱ የአካባቢውን አርሶ አደር ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ዓመቱን ሙሉ ለማምረት አስቻይ ሁኔታን ይፈጥራል። ይህም በአገር አቀፍ ደረጃ የተያዘውን በምግብ ራስን የመቻል፣ ለኢንዱስትሪና ለወጭ ንግድ የሚሆን ትርፍ የማምረት ግብን ለማሳካት አበርክቶው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል። በ52 ሚሊዮን ብር ወጪ የሚገነባው የመስኖ ፕሮጀክቱ ከ25 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ አስረድተዋል። ፕሮጀክቱ በተያዘለት ጊዜ በጥራት ተገንብቶ እንዲጠናቀቅም የአካባቢው ማህበረሰብና የወረዳው አስተዳደር የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ማድረግ እንዳለባቸውም አሳስበዋል። የመተማ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ግዛት ሰረፀ በበኩላቸው፤ ለፕሮጀክቱ መተግበሪያ የሚሆን በጀት አስቀድሞ የተያዘ በመሆኑ ግንባታውን በፍጥነት ለማከናወን ያስችላል ብለዋል። ከመስኖ ግንባታ ፕሮጀክቱ ጎን ለጎንም የአካባቢውን አርሶ አደሮች በማደራጀት ፈጥነው ወደ ልማት እንዲገቡ በማድረግ ለሌሎች አካባቢዎች የልማት ሞዴል እንዲሆኑ እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። በፀሐይ ኃይል (ሶላር ኢነርጂ) የሚንቀሳቀሰውን የመስኖ ፕሮጀክት በተያዘለት ጊዜና ጥራት ገንብቶ በፍጥነት ለማጠናቀቅ ይሰራል ያሉት ደግሞ የተቋራጩ ስራ አስኪያጅ ደምመላሽ ወርቁ ናቸው። ለግንባታው መፋጠን የአካባቢው ማህበረሰብና አስተዳደር ሰላሙን በመጠበቅ አጋዥ ሊሆኑ እንደሚገባም አመልክተዋል። በወረዳው የኩመር አፍጥጥ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ውበት መኮንን እንደገለፁት፤ ዓመቱን ሙሉ የሚፈስ ወንዝ ቢኖርም የመስኖ መሰረተ ልማት ባለመኖሩ በመስኖ ስራው ውጤታማ ሳይሆኑ ቆይተዋል። አሁን ላይ የመስኖ ግድብ መገንባቱ ከመኸር ልማቱ በተጨማሪ በበጋው ወቅትና ዓመቱን ሙሉ በማልማት ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እንደሚሰሩ ተናግረዋል። በዕለቱ የዞንና የወረዳ አመራሮች በተገኙበት ከተቋራጩ ጋር የውል ስምምነት ሰነድና የሳይት ርክክብ በይፋ ተፈጽሟል።
ሰመራ ዩኒቨርሲቲ በምርምር ዘርፍ የጀመራቸውን ሥራዎች በማጠናከር፣ የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ይሠራል
Jun 23, 2026 347
ሰመራ፣ሰኔ 16/2018(ኢዜአ)፡- ሰመራ ዩኒቨርሲቲ በምርምር ዘርፍ የጀመራቸውን ሥራዎች በማጠናከር፣ የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት እንደሚሠራ ተገለጸ። ዩኒቨርሲቲው የክልሉን የአምስት ዓመት የገቢ ጥናት ህትመት አጠናቆ በዛሬው ዕለት ለክልሉ ገቢዎች ቢሮ አስረክቧል። የአፋር ክልል ያለውን ሰፊ የኢኮኖሚና የንግድ አቅም በመጠቀም የውስጥ ገቢውን ማሳደግ እና የልማት ፕሮጀክቶችን በራስ አቅም መደገፍ ከክልሉ መንግስት ዋና ዋና ትኩረቶች መካከል አንዱ ነው። ይሁን እንጂ የገቢ አሰባሰብ ስርዓቱን ዘመናዊ ከማድረግ፣ የግብር ከፋዩን መሠረት በትክክል ከመለየት እና ሊሰበሰብ የሚችለውን እውነተኛ የገቢ አቅም በጥናት ላይ ተመስርቶ ከመተንበይ አኳያ ሰፊ ክፍተቶች ሲታዩ ቆይተዋል። ሰመራ ዩኒቨርሲቲ የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የክልሉን ሁለንተናዊ ዕድገት ለማገዝ ከወሰዳቸው ቁርጠኛ እርምጃዎች መካከል አንዱ የምርምር ስራዎቹን ከክልሉ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ፍላጎት ጋር ማጣጣም ነው። በተለይም የክልሉን የገቢ አቅም በሳይንሳዊ መንገድ ማጥናት የመንግስትን የፖሊሲ እና የውሳኔ አሰጣጥ አቅም ለማጠናከር ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ይታመናል። በዚህም መሰረት፣ ዩኒቨርሲቲው በምርምር ዘርፍ የጀመራቸውን ስራዎች ወደ ተግባር በመቀየር ረገድ ትልቅ ማሳያ የሚሆን ስራ አከናውኗል። ተቋሙ በክልሉ ያለውን የገቢ አሰባሰብ እና የወደፊት አቅጣጫ የሚያሳይ የአምስት ዓመት የገቢ ጥናት ህትመት አጠናቆ በዛሬው ዕለት ለክልሉ ገቢዎች ቢሮ ማስረከቡም የዚሁ ጥረት ማሳያ ነው። በርክክብ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ አወል አብዱ እንደተናገሩት፤ ዩኒቨርሲቲው ባስረከበው ጥናት መነሻነት ከወረዳ እስከ ቀበሌ የሚገኙ የክልሉን የገቢ ሀብቶች በትክክል መለየት ተችሏል። የጥናቱ ሪፖርት ከእንስሳት ሀብት ጀምሮ ያሉትን የተፈጥሮ ጸጋዎች ለመለየትና በሁሉም ወረዳዎችና ከተማ አስተዳደሮች በትኩረት መሥራት እንዲችሉ ትልቅ እገዛ ማድረጉንም አስረድተዋል። የክልሉን ሀብቶች አሟጦ ለመጠቀም ለሚደረገው ጥረት ጥናቱ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው የገለጹት ኃላፊው፤ የተገኘው የጥናት ውጤትም በተገቢው መንገድ ሥራ ላይ እንደሚውል አረጋግጠዋል። የዩኒቨርሲቲው የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ዓሊ በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው ለምርምርና ጥናት ሥራዎች ልዩ ትኩረት በመስጠት ለማኅበረሰቡ ተጠቃሚነት በትጋት እየሠራ ይገኛል። ይህ ጥናት የክልሉን የገቢ ምንጮች ለማስፋት፣ የታክስ አስተዳደሩን ለማዘመን እና በቀጣይ አምስት ዓመታት የሚሰበሰበውን ገቢ በዕቅድ ለመምራት እንደ ታላቅ መተግበሪያ የሚያገለግል መሆኑን ገልጸው፤ በተቋማቱ መካከል ያለውን የምርምርና የተግባር ትስስርንም ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋገረ ክንውን ነው ብለዋል። አቶ አደም እንደገለጹት፣ ዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ተኮር ሥራዎችን በትብብር እያሰፋ ይገኛል። ለዚህም ማሳያ የሚሆነው የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት (ከ2016 እስከ 2020 ዓ.ም) የሚጠቀምበት የገቢ ሀብት ጥናት ተጠናቆ መቅረቡ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት አቅም ወደ ተጨባጭ ብሔራዊ ዕድገት እየቀየረች ነው
Jun 23, 2026 184
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት አቅም ወደ ተጨባጭ ብሔራዊ ዕድገት እየቀየረች እንደምትገኝ የማዕድን ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሐና ብርሃኑ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ቃል የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ በመካሄድ ላይ ነው። የማዕድን ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሐና ብርሃኑ፣ በኢትዮጵያ የማዕድን ዘርፍ ከነበረበት ደካማ አፈጻጸም ተነስቶ አሁን ላይ የሀገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ስትራቴጂካዊ ምሰሶዎች አንዱ መሆን የቻለበትን የማዕድን ትራንስፎርሜሽን ጉዞ አቅርበዋል። በቁርጠኛ ማሻሻያዎች፣ በገበያ መልሶ ማዋቀር እና እሴትን መጨመር በሚያስችሉ ኢንቨስትመንቶች በመታገዝ ዘርፉ ከፍተኛ የወጪ ንግድ ገቢን እያስገኘ፣ የገቢ ምርቶችን ጥገኝነት እየቀነሰ እና ለኢንዱስትሪ ልማት አዳዲስ ዕድሎችን እየፈጠረ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በወርቅ፣ በወሳኝ ማዕድናት፣ በነዳጅ እና በማዳበሪያ ምርት ላይ እየተስፋፋ በመጣው የኢንቨስትመንት ለውጦች፣ ኢትዮጵያ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት አቅም ወደ ተጨባጭ ብሔራዊ ዕድገት እየቀየረችው ትገኛለች ብለዋል። ሚኒስትር ዴኤታዋ፤ እነዚህ ስኬቶችም በሀገር በቀል ቅኝት የሪፎርም ማሻሻያ፣ በገዘፈ ርዕይ እና አፈጻጸም ድምር ውጤት እንደሚያስገኙ ህያው ማረጋገጫዎች መሆናቸውን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ከእጅ ወደ አፍ ልምምድ ተላቆ ወደ ንግድና የሉዓላዊነት መሠረት ተሸጋግሯል
Jun 23, 2026 186
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ከእጅ ወደ አፍ ልምምድ ተላቆ ወደ ንግድና የሉዓላዊነት መሠረት ሽግግር ማድረጉን የግብርና ትራንስፎሜሽን ኢንስትቲዩት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) አመለከቱ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ቃል የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ እየተካሄደ ይገኛል። የግብርና ትራንስፎሜሽን ኢንስትቲዩት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በጉባኤው ላይ የግብርና ዘርፍ የለውጥ ጉዞን በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም ኢትዮጵያ ስልታዊ ኢንቨስትመንቶችን እና ጉልህ ማሻሻያዎችን በማከናውን የሀገሪቱን የግብርና ዘርፍ ከነበረበት ከእጅ ወደ አፍ ልምምድ ተላቃ አሁን ላይ ከእርሻ ወደ ንግድ ብሎም የሉዓላዊነት መሰረት የተሸጋገረ መሆኑን አመላክተዋል። ለዚህም ከ10 ዓመቱ መሪ እቅድ ጋር የተጣጣሙ ስትራቴጂዎችንና የፖሊሲ ለውጦ ማዕቀፎችን በመንደፍ፤ የመንግሥት፣ የግል ዘርፉንና የህዝብ አጋርነትን በማጠናከር፣ ፈጠራንና የግብርና ቢዝነስን በማስፋፋት እንዲሁም የምግብ ሉዓላዊነትን በማሳደግ የግብርናው ዘርፍ ይበልጥ ምርታማ፣ በገበያ ላይ የተመሰረተ እና ተፈጥሮአዊና ሰው ሰራሽ ቀውሶችን የመቋቋም አቅሙ የዳበረ እንደሆነ ገልጸዋል። ቀደም ሲል ከውጪ በሚገቡ ምርቶች ላይ በስፋት ተመርኩዛ የነበረችው ኢትዮጵያ አሁን ላይ በሀገር ውስጥ ተተኪ ምርቶችን በማሳደግ፣ የሌማት ትሩፋትና መሰል ሀገር በቀል ተነሳሽነቶችን በማዳበር፣ ቴክኖሎጂንና የሰው ሰራሽ አስተውሎትን በመታገዝ ለወጣቱ የስራ እድልን ከመፍጠር ባሻገር ሀገሪቱ በምግብ ራሷን ለመቻል ለምታደርገው ጉዞ አመርቂ ውጤት እያስገኘ እንደሚገኝ ዋና ሥራ አስፈፃሚው አስታውቀዋል። እነዚህ የታቀዱና መጻኢውን ጊዜ ያገናዘቡ ስልታዊ እርምጃዎች ለዘላቂ የግብርና አብዮት፣ ለገጠር ብልጽግና እና ለጠንካራ ኢኮኖሚ መሰረት እየጣሉ ሲሆን ይህም ኢትዮጵያ ወደፊት እየተራመደችና ተጨባጭ ለውጥ እያስመዘገበች መሆኑን በተግባር እንደሚያሳይ አመልክተዋል።
የምንገነባው መኖሪያ ቤት ብቻ ሳይሆን ክብራችንን የሚያስጠብቅ ምቹና ፅዱ አካባቢን ነው-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jun 23, 2026 153
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ የምንገነባው መኖሪያ ቤት ብቻ ሳይሆን ክብራችንን የሚያስጠብቅ ምቹና ፅዱ አካባቢን ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በመልዕክታቸው፤ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የዛሬ ሁለት ወር የተጀመረው የቅጠል ተራ የቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት በአስደናቂ ፍጥነት እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ከንቲባዋ ዛሬ በሳይቱ በመገኘት የግንባታውን ሂደት የገመገሙ ሲሆን፣ የዛሬ ሁለት ወር የተጀመሩት ህንጻዎች በአሁኑ ወቅት 9ኛ ወለል ላይ መድረሳቸውን ተመልክተዋል። ከቦታ ማጽዳት ስራዎች ጋር በተያያዘ የዛሬ ወር የተጀመሩት ህንጻዎች 4ኛ እና 5ኛ ወለል ላይ የደረሱ ሲሆን፣ ከሁለት ሳምንት በፊት የግንባታ ሂደቱን ከተመለከቱ በኋላ አዲስ የተጨመሩት የሶስት ህንጻዎች ጅማሮም በጥሩ ሂደት ላይ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በእነዚህ ፕሮጀክቶች የሚገነቡት መኖሪያ ቤቶች ብቻ ሳይሆኑ ለንግድ፣ ለጸጥታ፣ ለትምህርት ቤት እና ለጤና ተቋማት፣ ለስፖርት ማዘዉተሪያ፣ ለህፃናት መጫወቻ እና ለሌሎች ማህበራዊ አገልግሎት መስጫዎች እንዲሁም ለህዝብ የጋራ መገልገያዎች እኩል ትኩረት መሰጠቱን ነው ያብራሩት። በመሆኑም እየተገነባ ያለው መኖሪያ ቤት ብቻ ሳይሆን ህጻናት ቦርቀው የሚያድጉበት፣ ወጣቶች የአካልና የአዕምሮ ብቃታቸውን የሚያዳብሩበት፣ ዜጎች አገልግሎቶችን በቅርበት የሚያገኙበት እና ክብራቸውን የሚያስጠብቅ ምቹና ፅዱ አካባቢ መሆኑን አመልክተዋል። በአጠቃላይ የቅጠል ተራ መኖሪያ መንደርን ትናንት ከተጀመረው የገዳም ሰፈር እና በመሀሉ ላይ ከሚገኘው የጣልያን ሰፈር ጋር በማገናኘትና በማልማት፣ አካባቢውን የዘመነ አኗኗርና ሰፊ የስራ እድል የሚፈጥር ስፍራ ለማድረግ መታቀዱንም ነው የገለጹት። ከንቲባዋ አክለውም በምርጫ ወቅት ላይ ሆኖ የፕሮጀክቶቹ ግንባታ ሳይቀዛቀዝ መቀጠሉ፣ በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ ነዋሪዎችን በታማኝነት የማገልገል አቋማቸው ፅኑ መሆኑን የሚያሳይ መሆኑን ጠቁመዋል። ህንጻዎቹን በጥራት እና በፍጥነት ገንብተው በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ ሌት ተቀን እየሰሩ የሚገኙ አመራሮችን፣ ሰራተኞችን፣ ማህበራትን፣ ተቋራጮችን እና ሁሉንም ባለድርሻ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
በክልሉ ቡናን በክላስተር በማምረት ጥራቱንና የማሳ ሽፋኑን የማሳደግ ስራ እየተከናወነ ነው- ባለስልጣኑ
Jun 23, 2026 91
ሃዋሳ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል ቡናን በክላስተር በማምረት ጥራቱንና የማሳ ሽፋኑን የማሳደግ ስራ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ቡና ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን አስታወቀ፡፡ የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ መስፍን ቃሬ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ቡናን በክላስተር በማምረት የማሳ ሽፋን እና ጥራቱን የማሳደግ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለአብነትም በ2015 ዓ.ም በ25 ክላስተሮች የተጀመረው ቡናን የማልማት ስራ አሁን ላይ ወደ 239 ለማሳደግ መቻሉን ገልፀዋል። በዘንድሮው ዓመትም በእያንዳንዱ ቀበሌ ሁለት ሁለት ክላስተሮችን እንዲኖሩ በማድረግ ቡናን የማልማት ስራን ከፍ የማድረግ እቅድ ተይዞ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የቡና ማሳን ለማስፋት በየአመቱ የችግኝ ተከላ እንደሚካሄድ የገለጹት ዳይሬክተሩ በዘንድሮ ዓመት 36 ነጥብ 5 ሚሊዮን የቡና ችግኝ መተከሉን ገልፀዋል። በአሁኑ ወቅት የቡና ምርታማነት ማሻሻያ ፓኬጆችን ተግባራዊ በማድረግ በአለም አቀፍ ገበያ ተወዳሪ ለመሆን እየተሰራ መሆኑንም ገልፀዋል። በዘንድሮ ዓመት 31 ሺህ ሔክታር መሬት ላይ የሚገኙ ያረጁ ቡናዎች የማደስ ስራ መሰራቱንም ነው ያነሱት። በተለይም በክልሉ የሚመረተው ቡና ተፈጥሯዊ ጣእሙን የጠበቀ እንዲሆን የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘገጃጀትና አጠቃቀም ላይ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም ባለፉት ሁለት ዓመታት ከቡና ኢንዱስትሪዎች የሚወጣውን የቡና ገለፈት ወደ ተፈጥሮ ማዳበሪያነት የመቀየር ስራም እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ይህም ያጋጥም የነበረውን የአካባቢ ብክለት ከማስቀረት ባሻገር የቡና ጥራትና ምርታማነት በማረጋገጥ ረገድ ጉልህ ሚና የሚያበረክት እንደሆነም ገልፀዋል፡፡ በክልሉ ያሉ 220 የቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎቹ መደበኛና ቨርሚ ኮምፖስት አዘጋጅተው ለአርሶ አደሩ እንዲያቀርቡ መደረጉንም ነው የተናገሩት፡፡ በማእከላዊ ሲዳማ ዞን የዳሌ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ባልቻ በላይነህ በበኩላቸው፤ በወረዳው ከሚገኙ 32 ቀበሌዎች ውስጥ ሃያ አንዱ ሙሉ በሙሉ ቡና አምራች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ለዚህም በወረዳው የቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎችና በተደራጁ ወጣቶች የቡና ጥራት፣ምርታማነትና ተፈጥሮአዊ ጣእም የሚያስጠብቁ የተፈጥሮ ማዳበሪያ (ኮምፓስት) እያዘጋጁ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ይሕም ያጋጥም የነበረውን የአካባቢ ብክለት ከመከላከል ባለፈ ቡና ከአርሶ አደሩ ጋር ትስስር ለመፍጠር እና ጥራትን ለማስጠበቅ እያስቻለ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዳሌ ወረዳ የሾኤ ቀበሌው ሞዴል አርሶ አደር አሰፋ ደበቆ በ 3 ነጥብ 5 ሄክታር ማሳ ላይ ቡና እያለሙ መሆኑን ነው የሚናገሩት ፡፡ የቡና ጥራትና ምርታማነት ለማረጋገጥ ከችግኝ መረጣ እስከ ምርት አሰባሰብ ድረስ በባለሙያ የታገዘ እንክብካቤ እንደሚያደርጉ ገልጸው የተፈጥሮ ማዳበሪያ፣ጥላ ዛፍና ደባል ሰብሎችን እንደከተሉ ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ አዲስ የከተማ ልማት ምዕራፍ ውስጥ እየገባች ነው
Jun 23, 2026 114
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ አዲስ የከተማ ልማት ምዕራፍ ውስጥ እየገባች እንደምትገኝ በገንዘብ ሚኒስቴር ከፍተኛ አማካሪ የሆኑት ትዕግሥት ፍስሀ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ቃል የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ እየተካሄደ ነው። በገንዘብ ሚኒስቴር ከፍተኛ አማካሪ የሆኑት ትዕግሥት ፍስሀ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ አዲስ የከተማ ልማት ምዕራፍ ውስጥ እየገባች መሆኑን አመልክተዋል። የልማቱ ትኩረት ከተሞችን ምቹ፣ ተወዳዳሪ፣ ሁሉን አቀፍና ዘመናዊ ማድረግ ነው ብለዋል። አማካሪዋ አክለውም ይህም ከተሞች ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለጋራ ብልፅግና ቀጣይ ሞተር እንዲሆኑ የማድረግ ውጥን እንዳለውም አብራርተዋል፡፡
የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገር ውስጥ መረጋጋትንና ተዓማኒነትን መልሶ እንዲመጣ አድርጓል- የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)
Jun 23, 2026 142
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፦የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገር ውስጥ መረጋጋትንና ተዓማኒነትን መልሶ ማምጣቱን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ቃል የ“ኢትዮጵያ ታከናውናለች” ጉባኤ እየተካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያ የሀገር ውስጥ መረጋጋትንና ተዓማኒነትን መልሶ ማምጣቱን ገልጸዋል። ይህ ውጤት የተገኘው የዋጋ ንረትን በመቆጣጠር፣ የውጭ ምንዛሪ ገበያውን ነፃ በማድረግ፣ የገንዘብና የፊስካል ፖሊሲን በማዘመን፣ እንዲሁም ለዘላቂና አካታች ዕድገት ጠንካራ መሠረት ለመጣል የፋይናንስ ዘርፉን በማጠናከር መሆኑን አብራርተዋል።
የወላይታ ሶዶ ከተማ የኮሪደር ልማትን በተያዘለት የጊዜ ገደብ ለማጠናቀቅ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jun 23, 2026 141
ወላይታ ሶዶ፤ ሰኔ 16/2018 (ኢዜአ)፡-የወላይታ ሶዶ ከተማ የተቀናጀ የኮሪደር ልማት ሥራን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑ ተገለጸ፡፡ የወላይታ ሶዶ ከተማ ማዘጋጃ ቤት የተቀናጀ መሠረተ ልማት አቅርቦት ሥራ ሂደት አስተባባሪ አቶ አስራት ዳዊት ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በከተማዋ በአዲስ መልክ የተጀመረው 4 ኪሎ ሜትር የተቀናጀ የኮሪደር ልማት ሥራ በልዩ ትኩረት እየተመራ ነው። የኮሪደር ልማት ሥራው የመኪና፣ የእግረኛና የብስክሌት መንገድ እንዲሁም የተለያዩ የመንገድ ዳር ማረፊያዎችንና መዝናኛ ቦታዎችን አካቶ እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል። የኮሪደር ልማቱን በተያዘለት የጊዜ ገደብ ለማጠናቀቅ ቀጣይነት ባለው ሁኔታ ምሽትና ቀን የሚሰራው ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉንም ገልጸዋል። አራት ኪሎ ሜትር ለሚሸፍነው የኮሪደር ልማት ከ5ዐዐ ሚሊዮን ብር በጀት መያዙን የገለጹት አቶ አስራት፣ የግንባታ ሥራው በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅም ተናግረዋል፡፡ ልማቱ ተጠናቅቆ ለአገልግሎት ሲበቃ የከተማዋን ውበትና ገጽታ ከማሳደግ በተጨማሪ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴን በማሳለጥ ረገድ አበርክቶው የጎላ መሆኑን አስታውቀዋል። በተጨማሪም የኮሪደር ልማቱ የቱሪስት ፍሰትን ለማሳደግ፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠር እና የከተማዋን ገቢ ለማሳደግ ጠቀሜታው ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የከተማዋን የኮሪደር ልማት ሥራ እያከናወነ የሚገኘው ወርልድ ጠቅላላ ሥራ ተቋራጭ ባለቤት አቶ ፍቅሬ ብርሃኔ በበኩላቸው እንዳሉት የኮሪደር ልማቱን በተያዘለት የጊዜ ገድብ ለማጠናቀቅ ምሽትና ቀን እየተሰራ ነው፡፡ አስካሁን በኮሪደር ልማቱ ከ200 ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸው፣ ስራውን በፍጥነትና በጥራት ለማጠናቀቅ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የኮሪደር ልማቱ የሥራ ዕድል እንደፈጠረላቸው የተናገሩት ደግሞ አቶ እሸቱ በዛ እና ወጣት ፈቃዱ መኮንን የተባሉ የከተማዋ ነዋሪ ናቸው። ሥራው ከቀን ባለፈ ምሽት ጭምር መከናወኑ የሥራ ባህላቸውንእንደቀየረውና ይበልጥ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል፡፡
በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የተተከሉ ችግኞች የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እያደረጉን ነው
Jun 23, 2026 110
አዳኝ አገር ጫቆ፣ሰኔ16/2018(ኢዜአ)፡-በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ቀደም ሲል የተተከሉ ችግኞች የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እያደረጓቸው መሆኑን በምዕራብ ጎንደር ዞን የአዳኝ አገር ጫቆ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ። አርሶ አደሮቹ እንዳሉት ቀደም ሲል በአካባቢያቸው የተከናወኑ የችግኝ ተከላና የእንክብካቤ ሥራዎች የአፈርና የውሃ ሀብትን በመጠበቅ ለአካባቢው ግብርና መነቃቃትና ለተጠቃሚነታቸው ማደግ ጉልህ አስተዋፅኦ አበርክተዋል። በቀጣይም ይህን ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደገ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች ለመትከል መዘጋጀተቸውን ተናግረዋል። ከወረዳው አርሶ አደሮች መካከል አቶ ሙሉነህ ጀምበር እንደገለጹት፣ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት በአካባቢያቸው ላይ ከፍተኛ ለውጥ በማምጣት ተጠቃሚ አድርጓቸዋል። ቀደም ሲል በድርቅና በአፈር መሸርሸር ተጎድቶ የነበረው መሬት ማገገሙና የከርሰ ምድር ውሃ መጨመሩ አትክልትና ፍራፍሬ በመስኖ አልምተው ተጠቃሚ ለመሆን እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። ይህን ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግም በመጪው ክረምት በወል መሬት ላይ ከሚተክሉት የደን ችግኞች በተጨማሪ በራሳቸው ግማሽ ሄክታር የሚጠጋ መሬት ላይ ማንጎና ዘይቱን ለመትከል ችግኝ ማዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ሌላኛው የወረዳው አርሶ አደር ተሾመ ጫንያለው በበኩላቸው እንዳሉት የአረንጓዴ ልማቱ የእንስሳት መኖ ልማት፣ የንብ ማነብና ሌሎች የገቢ ማስገኛ ሥራዎችን በማከናወን ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኙ አስችሏቸዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ቀደም ሲል የተከሏቸው ማንጎና ሌሎች የቆላ ፍራፍሬ ችግኞች አሁን ላይ ምርት መስጠት በመጀመራቸው ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። አርሶ አደር ታረቀኝ ታከለ በበኩላቸው፣ ዘንድሮ የሚተከሉ ችግኞችን በማዘጋትና የመትከያ ጉድጓዶችን በወቅቱ በመቆፈር በቂ ዝግጅት ማድረጋቸውን ገልጸዋል። በመጀሪያው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተከሉት የቡና ችግኝ በአሁኑ ወቅት ምርት መስጠት በመጀመሩ ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ከምርቱ ሽያጭ ከ70ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ያገኙትን ጥቅም ለማስፋትም በክረምት በሚካሄደው የችግኝ ተከላ በንቃት ለመሳተፍ የጉድጓድ ቁፋሮ ሥራውን ቀድመው ማጠናቀቃቸውን ገልጸዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ፈንታሁን ኪሮስ በበኩላቸው እንዳሉት በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች ለመትከል እየተሰራ ነው። ባለፈው ዓመት ከተተከሉ ችግኞች ውስጥ 70 በመቶ የሚሆኑት መጽደቃቸውን አስታውሰው፣ለእዚህም ማህበረሰቡ ለተተከሉ ችግኞች የሚያደርገው እንክብካቤ እያደገ መምጣት አስተዋጾ አድርጓል ብለዋል። በዘንድሮ ክረምትም ለአካባቢው ስነ ምህዳር ተስማሚ የሆኑ የደንና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የቆላ ፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል ሰፊ ዝግጅት መደረጉን አመልክተዋል። ለተከላ ከተዘጋጁ ችግኞች ውስጥ አካሻ ሰኔጋል፣ ሽመል (የቆላ ቀርቀሃ)፣ ኒም፣ ሞሪንጋ፣ ማንጎ፣ ፓፓያ፣ ሙዝ እና ሌሎች እንደሚገኙበት የጠቆሙት አቶ ፈንታሁን፣ ለእዚህም ከ200 ሺህ በላይ ጉድጓዶች ተቆፍረዋል ብለዋል።
ዘላቂ ለውጥ የሚመጣው በጋራ በመቆም ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jun 23, 2026 157
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 16/2018(ኢዜአ) ፦ ሀገርን መገንባት በአንድ ትውልድ ብቻ የሚያበቃ ሳይሆን የሁላችንም የጋራና ቀጣይነት ያለው ሥራ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። “ኢትዮጵያ ታከናውናለች” የተሰኘ ብሔራዊ ጉባኤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት እየተካሔደ ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት “ኢትዮጵያ ታከናውናለች” በተሰኘው ብሔራዊ ጉባኤ ላይ በመገኘቴ ታላቅ ክብር ይሰማኛል ሲሉ ገልጸዋል። “ከለውጥ ወደ ዘላቂ ሽግግር” በሚል መሪ ቃል እየተካሄደ ባለው ጉባኤ ላይ፣ በየደረጃው የተጓዝንበትንና አሁን የደረስንበትን መንገድ መለስ ብዬ እንድቃኘው አድርጎኛል ሲሉም ገልጸዋል። ሀገራችን በራሷ አቅም ታላቁን የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በመገንባት፣ ያልተሞከሩ ግዙፍ ልማቶችን በማከናወን በየጊዜው ወደ ላቀ ደረጃ እየተሸጋገረች ትገኛለች ብለዋል። እነዚህ ሁሉ በአጋጣሚ የተገኙ ድሎች አይደሉም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመደመር መንፈስ ላይ ተመስርተው፣ ዘላቂ ለውጥ የሚመጣው በጋራ በመቆም ነው በሚል ጽኑ እምነት የተወሰዱ በቆራጥ ውሳኔዎች የተገኙ ውጤቶች ናቸው ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አያይዘውም የጀመርናቸው ለውጦች በራሳቸው የመጨረሻ ግብ አይደሉም ይልቁንም ከእኛ በኋላ ለሚመጡት ተከታታይ ትውልዶች የምንጥለው ጠንካራ መሠረት ነው ብለዋል። ሀገርን መገንባት በአንድ ትውልድ ብቻ የሚያበቃ ሳይሆን የሁላችንም የጋራና ቀጣይነት ያለው ሥራ በመሆኑ፤ በዚህ ጽኑ እምነት እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ይህንን መንፈስ ይዞ ወደፊት እንዲጓዝ፣ የተቀበለውን ወረት አግዝፎ ይበልጥ ወደ ላቀ ከፍታ እንዲያመራ ጥሪዬን አቀርባለሁ ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።