ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በሐረሪ ክልል በቱሪዝም ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ቅርሶችን በመታደግ የሐረርን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻነት እያጎለበቱ ነው
Jul 2, 2026 10
ሐረር፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- በሐረሪ ክልል በቱሪዝም ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ቅርሶችን በመታደግ የሐረርን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻነት ማጎልበቱን የክልሉ ቱሪዝም ኮሚሽን ገለጸ። መንግሥት ያዘጋጀው የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ-ግብር ከለያቸው አምስት ቁልፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ምሰሶዎች መካከል ቱሪዝም አንዱ ነው። ከዚህ ቀደም ዘርፉ በበቂ ሁኔታ ሳይለማና የገቢ ምንጭነቱ ሳይጎለብት በመቆየቱ፣ አሁን ላይ ሀገራዊ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ እና የሥራ ዕድል ለመፍጠር እንደ ዋና ሞተር ተለይቶ እየተሰራበት ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል በሰጡት ማብራሪያም በዘርፉ ልማት የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው፤ የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በማሳያ አስቀምጠዋል። የጥንት ውበታቸውን ከዘመናዊ ገጽታ ጋር በማሰናሰል የቱሪዝም መዳረሻ እንዲሆኑ በለውጡ መንግሥት እንደ አዲስ ከተገነቡና ከተሻሻሉ የኢትዮጵያ ከተሞች መካከል ጥንታዊቷና ታሪካዊቷ የሐረር ከተማ ቀዳሚዋ ነች። የሐረር ጀጎል ግንብና በውስጡ የሚገኙት ጥንታዊ፣ ሃይማኖታዊና ታሪካዊ ቅርሶች ከኢትዮጵያ አልፎ የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ሀብት መሆናቸው ይታወቃል። በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ እየተተገበረ ያለው የኮሪደር ልማትና የቅርሶች እድሳት ስራ፣ የታሪካዊቷን ሐረር ከተማ የቱሪዝም ዘርፍ ይበልጥ በማነቃቃት ለአካባቢያዊና ሀገራዊ ኢኮኖሚው አዲስ አቅም እየፈጠረ ይገኛል። የክልሉ የቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሚ አብዱልዋሲ እንደገለጹት፣ በክልሉ ያለውን የቱሪዝም ዘርፍ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገርና እምቅ አቅሙን ለመጠቀም መጠነ-ሰፊ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። የቱሪዝም ዘርፉን ለማጎልበት የተከናወኑት ተግባራትም ለአደጋ ተጋርጠው የነበሩ ቅርሶች እንዲለሙና ይዘታቸውን ጠብቀው ለትውልድ እንዲተላለፉ ማስቻላቸውን ኮሚሽነሩ ገልጸው፤ ይህም ለዘርፉ መነቃቃት ትልቅ አቅም ፈጥሯል። በዘርፉ በተሰጠው ትኩረት የቱሪዝም መስህቦችን በማልማት፣ የጎብኚዎችን ቆይታ በማራዘምና ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ አቅም በማሳደግ ረገድ የተሻሉ ተግባራት የተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮ ዓመት ክልሉን የጎበኙ የውጭ ቱሪስቶች ቁጥር ካለፈው ዓመት የ47 በመቶ ብልጫ ማሳየቱን የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ ይህም መሠረተ-ልማቶች ሲሟሉ የቱሪዝም ዘርፉ የኢኮኖሚው ዋነኛ ምሰሶ እንደሚሆን አመላካች ነው ሲሉ ተናግረዋል። እንደ አቶ ሳሚ ገለጻ፣ የቱሪዝም ዘርፉን ለማጎልበት የተከናወኑት ተግባራት ከውጭ ሀገር ቱሪስቶች ባሻገር የሀገር ውስጥ ጎብኚዎች፣ የማኅበራዊ ሚዲያ አንቂዎችና ሌሎች አካላት ሐረርን እንዲጎበኙና ውበቷን ለዓለም እንዲያስተዋውቁ ሰፊ ዕድል ፈጥሯል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በተያዘው ክረምት በ100 ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ በኩታ ገጠም ይተከላል
Jul 2, 2026 23
ደብረ ማርቆስ ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):-በምስራቅ ጎጃም ዞን በተያዘው ክረምት በ100 ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ በኩታ ገጠም እንደሚተከል የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የአትክልትና ፍራፍሬ ባለሙያ አቶ ተሾመ በላይ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለቡና ልማት ስራ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በዞኑ በያዝነው ክረምት በቡና ከሚለማው አጠቃላይ ከ320 ሄክታር መሬት ውስጥ ከ100 ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት በኩታ ገጠም የሚለማ መሆኑን ገልጸዋል። በአጠቃላይ በበጋው ወቅት ከተዘጋጀው ከ916 ሺህ በላይ የቡና ችግኝ ውስጥም ከ330 ሺህ በላይ የሚሆነው ለኩታ ገጠም ልማት እንደሚውል ተናግረዋል። የቡና ኩታ ገጠም ልማቱ የሚካሄደውም ተስማሚ ስነ ምህዳርና የአየር ንብረት ባላቸው በደብረ ኤሊያስ፣ በማቻከልና ጎዛምን ወረዳዎች መሆኑን አመላክተዋል። በዞኑ በሚካሄደው የቡና ልማትም ከ690 በላይ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ እንደሚገኙ አስረድተዋል። በዞኑ የጎዛምን ወረዳ የሊባኖስ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ክብረት በዛበህ ፤ በተያዘው ዓመት ቡናን በኩታ ገጠም መትከል መጀመራቸውን ነው የሚናገሩት። ከዚህ በፊት ቡናን በጓሯቸው በማልማት ለቤት ውስጥ ፍጆታ ይጠቀሙ እንደነበር አስታውሰው በአሁኑ ወቅም ከግማሽ ሄክታር በላይ የሚሆን መሬት ላይ ቡናን በኩታገጠም በማልማት ለገበያ ለማቅረብ እየሰራሁ ነው ብለዋል። የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መንግስቱ ክፍሌ በበኩላቸው እንደሌሎች ሰብሎች ቡናን በኩታ ገጠም ለማልማት ከግማሽ ሄክታር በላይ መሬት በማዘጋጀት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም የማሳ ዝግጅት በማጠናቀቅ በጋራ የሚተከልበትን ቀን በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል።
የሸገር ከተማ አስተዳደር በበጀት ዓመቱ 37 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ ሰብስቧል
Jul 2, 2026 65
ሸገር፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- የሸገር ከተማ አስተዳደር በበጀት ዓመቱ 37 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን የከተማው የገቢዎች ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የሸገር ከተማ አስተዳደር በኦሮሚያ ክልል ልዩ ልዩ ወረዳዎችንና ከተሞችን በማጣመር በቅርብ ዓመታት የተመሰረተ ሰፊና አዲስ ከተማ ነው። ከተማው ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ ግዙፍ የኮሪደር ልማት፣ የመሰረተ ልማት ዝርጋታና የከተማ ውበት ፕሮጀክቶችን በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። እነዚህን ሰፊ የልማት ፍላጎቶች በራስ አቅም ለመደገፍና የከተማውን ሁለንተናዊ እድገት ለማፋጠን የውስጥ ገቢ አቅምን ማሳደግ ቀዳሚው የቤት ስራ ሆኖ ቆይቷል። ጽሕፈት ቤቱ በበጀት ዓመቱ የሰበሰበው ይህ ከፍተኛ ገቢ፥ የከተማዋን የልማት ፕሮጀክቶች በራስ አቅም ለመሸፈንና የህዝብን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ እየተደረገ ላለው ጥረት ትልቅ ስኬት እንደሆነ ይታመናል። የከተማ አስተዳደሩ ገቢዎች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መልካሙ አምባው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተማ አስተዳደሩ በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ 39 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ነበር። በበጀት ዓመቱም ከተለያዩ የገቢ ምንጮች 37 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ በመሰብሰብ የዕቅዱን 95 በመቶ ማሳካት መቻሉን ተናግረዋል። የገቢ አሰባሰብ ሂደቱ ስኬታማ የሆነው የታክስ አሰባሰብ ሥርዓትን ማሻሻልና ለዘርፉ ልዩ ትኩረት መሰጠቱ እንዲሁም ለግብር ከፋዮች ቀጣይነት ያለው ግንዛቤ መፍጠር በመቻሉ ነው ብለዋል። ከዚህም ባለፈ ሕጋዊ ደረሰኝ የመቁረጥ ልምድን ማሳደግ፣ ቴክኖሎጂን በማስፋት ግብር ከፋዮች ግብራቸውን ግልጽና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ እንዲከፍሉ ምቹ ሁኔታ በመፈጠሩ መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ከ400 በላይ ከፍተኛ ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው በዲጂታል መንገድ የሚጠበቅባቸውን ግብር እና ክፍያዎች መፈጸም መቻላቸውን ገልጸዋል። ይህንን የዲጂታላይዜሽን ሥርዓት ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግና ወደ ሙሉ ሥራ ለማስገባት ለባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ሥልጠና እየተሰጠ መሆኑን ኃላፊው አብራርተዋል። የዘርፉን አዋጆችና መመሪያዎች በመከተል እንደ ታክስ ስወራ ያሉ ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴዎችን ለመቆጣጠር የተቀናጀ ኮሚቴ ተዋቅሮ ክትትል እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ሕገ-ወጥነትን ለመከላከል በተሰሩ ሥራዎችም በበጀት ዓመቱ በሕገ-ወጥ መንገድ ሲንቀሳቀሱ የተገኙ ስድስት ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊ እርምጃ መወሰዱን አስታውሰዋል። በተጨማሪም ሕጋዊ ደረሰኝ ባለመቁረጣቸው ምክንያት በ240 ነጋዴዎች ላይ የገንዘብና አስተዳደራዊ ቅጣት መጣሉን ገልጸው፤ በቀጣይም የዲጂታል አሠራርን በማዘመንና በደንበኞች ዘንድ ግንዛቤ በመፍጠር ላይ ትኩረት ተደርጎ እንደሚሠራ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ የባሕር በር ብታገኝ የሚጠቀም እንጂ የሚጎዳ ሀገር እንደሌለ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ተገንዝቧል
Jul 2, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታሪካዊ፣ ሕጋዊና መልክዓ ምድራዊ መሰረት ያለው የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው ወሳኝ አጀንዳ መሆኑን ምሁራን ገለጹ። ምሁራኑ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት መብት ለማስከበር የሚከናወኑ ተግባራት ሳይንሳዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገድን የተከተሉ ናቸው። የሀገር ውስጥ ባንዳና የውጭ ባዕዳን ኃይሎች ኢትዮጵያ ላለፉት ሦስት አሥርት ዓመታት በላይ ከተፈጥሯዊና ታሪካዊ የባሕር በር ባለቤትነት ተነጥላ እንድትቆይ ማድረጋቸው ይታወሳል። ከሀገራዊ ለውጡ ማግስት የመደመር መንግሥት የትውልድን የተዳፈነ ጉዳይ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም አጀንዳ በማድረግ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ወደ ዓለም አቀፍ ቅቡልነት አሸጋግሯል። በኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማሲና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር እንዳለ ንጉሴ፤ የባሕር በር ባለቤትነት የሀገርን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት የሚያረጋግጥ የብሔራዊ ጥቅም ማዕከል ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከታሪካዊ፣ መልክዓ ምድራዊና ሕጋዊ መሠረት ባሻገር ብሔራዊ ጥቅምንና አዳጊ የሀገርና የዜጋ ፍላጎትን ማዕከል ያደረገ ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም ሕዝብና መንግሥት የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ምላሽ ለማስገኘት በውጤታማ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ በተደገፈ ሳይንሳዊ የዲፕሎማሲ መርህ ወደ ዓለም አቀፍ ቅቡልነት ማሸጋገራቸውን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነትም ሀገርን ከተፈጥሯዊ ማንነቷ በማስታረቅ ቀጣናዊ ሰላምና ደኅንነትን ዕድገትና ብልፅግናን የሚያረጋግጥ ወሳኝ የትብብር ዕድል መሆኑን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የባሕር በር ብታገኝ የሚጠቀም እንጂ የሚጎዳ ሀገር እንደሌለ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ መገንዘቡንም ነው ያነሱት። ኢትዮጵያ ጫናን በመቋቋም በዲፕሎማሲ ስኬት ሕዳሴ ግድብን ዕውን በማድረግ ቀጣናዊ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ትስስርን በመፍጠር ተምሳሌታዊነቷን በተግባር እያስመሰከረች እንደምትገኝም ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያንም ሕዳሴን በትብብር እንዳሳኩት ሁሉ፤ አንድነትን በማጠናከር የትውልድ ጥያቄ የሆነውን የባሕር በር ባለቤትነት ለማስከበር በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ ገልጸዋል። በዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ የሥነ-አመራርና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህሩ ጌትዬ ትርፌ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችው በውጭ ታሪካዊ ጠላቶችና በውስጥ ባንዳዎች ጥምር ሴራ ነው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከባሕር በር ባለቤትነቷ እንድትርቅ የተፈጸመባት ኢ-ፍትሐዊ በደል ቀጣናውን የሽብርተኞች መፈንጫ በማድረግ የጋራ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያቀጨጨ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ብሔራዊ ጥቅምን የማስከበር የህልውና ጉዳይ ሆኖ መቅረቡም ቅቡልነት ያለው አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል።
የእርሻ ስራን በግብርና ባለሙያ በመታገዝ በማከናወናችን ምርታማነታችን አድጓል-የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች
Jul 2, 2026 92
ወልቂጤ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- የመኸር ወቅት የእርሻ ስራን በግብርና ባለሙያዎች በመታገዝ እያከናወኑ በመሆኑ ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱን የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። የዞኑ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በግብርና ባለሙያዎች እየተደረገላቸው ያለው ድጋፍ የተቀናጀ የግብርና ስነ-ዘዴን በመጠቀም በእንስሳት እርባታም ጭምር ውጤታማ ሆነዋል። የእርሻ ስራን በግብርና ባለሙያዎች በመታገዝ እያከናወኑ በመሆኑ ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱንም አርሶ አደሮቹ ገልጸዋል። የአበሽጌ ወረዳ ነዋሪው አርሶ አደር ሰብስቤ ወልደሃዋርያት፤ አሁን ላይ ለዘር ምቹ ወቅት በመሆኑ በግብርና ባለሙያዎች ታግዘው የግብርና ልማት ሥራቸውን እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም እስካሁን ሁለት ሄክታር መሬታቸውን በበቆሎ ዘር መሸፈናቸውንና አንድ ሄክታሩን ደግሞ በጤፍ ለመሸፈን መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። በዞኑ የጌታ ወረዳ አርሶ አደር ጀማል ሟናጋ በበኩላቸው፤ ድንችን በአንድ ሄክታር መሬት ላይ ተክለው በመንከባከባቸው ለምግብ ፍጆታ የሚውል ምርት ከማምረት ባለፈ ለገበያ ጭምር በማውጣት ትርፋማ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ቀሪ አንድ ሄክታር ከግማሽ መሬታቸውን አርሰው በማለስለስ ሰብል ለመዝራት መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል። የሚደረግላቸው ሙያዊ ድጋፍ ምርታማነታቸውን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የተሳካ ስራ እንዲሰሩ ምክንያት እንደሆነ የገለፁት ደግሞ አርሶ አደር ገብሬ ዛጋ ናቸው። የተቀናጀ የግብርና አሰራርን በመከተል የተለያዩ ሰብሎችን በማልማትና እንስሳትን በማርባት ተግባር ላይ መሰማራታቸው የተሻለ ኑሮ እንዲመሩ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። ዘንድሮም ካላቸው የእርሻ መሬት ላይ አንድ ሄክታር መሬት በገብስ ለመሸፈን መዘጋጀታቸውን ጠቅሰው ለዚህም የአፈር ማዳበሪያ እና ምርጥ ዘር እንደቀረበላቸው ተናግረዋል። የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ፤ በዞኑ በተያዘው መኸር ከ43 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ዘር መሸፈኑን ተናግረዋል። በመኸር እርሻ 180 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት መታረሱን ገልፀው እስካሁን 160 ሺህ የሚጠጋ ማሳ መልማቱን አስረድተዋል። የግብርና ሜካናይዜሽንን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማላቅ እየተሰራ ያለው ስራ የዘርፉን ውጤታማነት እያሳደገው መሆኑንም አቶ አበራ አመልክተዋል።
በደቡብ ወሎ ዞን ከ 46 ሺህ በላይ ለሚሆኑ አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ተሰጠ
Jul 2, 2026 105
ደሴ ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- በደቡብ ወሎ ዞን ከ46 ሺህ በላይ ለሚሆኑ አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ መስጠቱን የዞኑ መሬት መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የገጠር መሬት አስተዳደር ቡድን መሪ አቶ ምሳው አክቤ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በዞኑ የሚገኙ አርሶ አደሮችን ዘላቂ የመሬት ባለቤትነት ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ውጤታማ ናቸው። ከዚህ ውስጥም በበጀት ዓመቱ ለ46 ሺህ 311 አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ በመስጠት መሬታቸውን በዘላቂነት አልምተው እንዲጠቀሙ ተደርጓል ነው ያሉት። የይዞታ ካርታው የአርሶ አደሩን ይዞታ በሳይንሳዊ መንገድ በመለካትና ማረጋገጫ በመስጠት የብድርና ሌሎች አገልግሎቶችን ለማግኘት ሰፊ እድል የፈጠረ እንደሆነም አስረድተዋል። በተጨማሪም አርሶ አደሩ በይዞታው በሚያገኘው የብድር አገልግሎት የግብርና ስራውን ለማዘመን የሚያስችለው ከመሆኑ ባለፈ ሌሎች የገቢ ማስገኛ ስራዎች ላይ እንዲሰማራ የሚያደርግ ነው ብለዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ ብቻ አራት ሺህ 693 አርሶ አደሮች ከ127 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉን አስረድተዋል። በዞኑ ደሴ ዙሪያ ወረዳ የ032 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መሀመድ ሰይድ ፣የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ማግኘቴ መሬቱን በተሻለ መንገድ ለማልማትና ተጨማሪ ሀብት ለማፍራት አስችሎኛል ብለዋል። ቀደም ሲል የነበረው ይዞታ ትክክለኛ ልኬት ያልነበረው በመሆኑ ከሌላ ባለመብት ጋር የመገፋፋት ሁኔታ ይፈጠር እንደነበር አስታውሰው ፣ አሁን ችግሩ ሙሉ ለሙሉ መፈታቱን ገልጸዋል። "የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታው ወሰንና ልኬትን በትክክል ያስቀመጠ በመሆኑ የመሬታችንን ዘላቂ ዋስትና ያረጋገጠ ነው" ያሉት ደግሞ የወረኢሉ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ጀማል ዋሴ ናቸው። ይህም ይገባኛል በሚል ይፈጠሩ የነበሩ ግጭቶችንና አለመግባባቶችን በማስቀረቱ ምርታማነታችን ለመጨመር ያግዘናል ነው ያሉት። በደቡብ ወሎ ዞን ባለፈው በጀት ዓመት ከ61 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የመሬት ማረጋገጫ ካርታ መስጠት መቻሉን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት በቱሪዝም ዘርፍ በተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት ታይቷል
Jul 2, 2026 183
ሮቤ ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):-በኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በቱሪዝም ልማት ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭና አበረታች ውጤት ማስመዝገባቸውን የዘርፉ ምሁራን አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል በሰጡት ማብራሪያ በዘርፉ ልማት የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በማሳያ አስቀምጠዋል። በተለይም በባሌ አካባቢ የሚገኙ የሶፍ ኡመር ዋሻ፣ ድሬ ሼህ ሁሴን፣ ባሌ ተራሮችን ጨምሮ ሌሎች የገበታ ለሀገር ፕሮጀክቶች ግንባታ፣ የከተሞች ኮሪደር ልማትና የቅርሶች እድሳት ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ትልቅ አቅም መሆናቸውን አብራርተዋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የቱሪዝም ዘርፍ መምህራንና ተመራማሪዎች እንዳሉት፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የባሌ ዞንን እምቅ የቱሪዝም አቅም በልዩ ሁኔታ የገለጹበት መንገድ ለዘርፉ መነቃቃት ከፍተኛ መሠረት የሚጥል መሆኑን ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው መምህርና የዘርፉ ተመራማሪ ስንታየሁ አይናለም(ዶ/ር) እንዳሉት፤ የባሌ ዞን የተለያዩ ሥነ-ምህዳሮች በአንድ ላይ የሚገኙበት መሆኑ ለቱሪዝም ዘርፉ ትልቅ አቅም መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይም መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት የቱሪዝም መስህቦችን በማልማት፣ የጎብኚዎችን ቆይታ በማራዘምና ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ በማሳደግ ረገድ የተሻሉ ተግባራት የተከናወኑበት መሆኑን ምሁሩ ገልጸዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የቱሪዝም ልማት ኢኒሼቲቮች አጠቃላይ የቱሪዝም ዘርፉን እያነቃቁት መሆኑን የጠቀሱት ተመራማሪው፤ ዩኒቨርሲቲው በዘርፉ የሚታዩ ተግዳሮቶችን በምርምር ለመለየት የአምስት ዓመት ሜጋ ፕሮጀክት ጥናት እያካሄደ እንደሚገኝም አስታውሰዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዞኑን እምቅ አቅም በይፋ መጥቀሳቸው፣ ለዘርፉ መነቃቃት ትልቅ አቅም መሆኑን ገልጸው፤ የግንባታ ሥራቸው የተጀመሩ የቱሪዝም መሠረተ ልማቶች ሲሟሉ ዘርፉ የኢኮኖሚው ምሰሶ እንደሚሆን ገልጸዋል። የባሌ ዞን ብዙም ባልተራራቁ አካባቢዎች የተለያዩ ዓይነት ሥነ-ምህዳሮች በቀላሉ የሚታዩበትና ለቱሪስት ተመራጭና ተወዳጅ የሆኑ ቅርሶች መገኛ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የዩኒቨርሲቲው መምህርና ተመራማሪ ሀዲስ ታደለ(ዶ/ር) ናቸው። የለውጡ መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት የእነዚህን መስህቦች ልማት ወደ ተግባር በማስገባት ላይ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም የቱሪስቶችን የቆይታ ጊዜ በማራዘም ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ እንደሚያግዝ ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲ ደረጃም ከዚህ በፊት በዋናነት ከሚታወቁት ዋና ዋና ቅርሶች ባሻገር ከ100 በላይ አዳዲስ ቅርሶች በጥናት መለየታቸውንና የተለዩት ቅርሶችም በሳይንሱ ዓለም እንዲታወቁ ዲጂታል ካርታ የተዘጋጀላቸው መሆኑን አመልክተዋል። በተለይም የዩኒቨርሲቲ ምሁራን እያካሄዱ በሚገኙት ጥናት በባሌ፣ ምሥራቅ ባሌና ምዕራብ አርሲ አካባቢ የሚገኙ የተለያዩ የተፈጥሮ፣ ሰው ሰራሽና ታሪካዊ የመስህብ ስፍራዎች ተለይተው፣ ዶክመንት ተሰንዶላቸው መቀመጣቸውን ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል። በአጠቃላይ፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የቱሪዝም ኢኒሼቲቭ ለዘርፉ ትልቅ መነሳሳትን የፈጠረ መሆኑን የጠቆሙት ምሁራኑ፣ የባሌ ዞንን የተፈጥሮና ባህላዊ ሃብቶችን በማዘመንና በምርምር በማገዝ የሀገሪቱን የቱሪዝም ገጽታ ለመቀየር በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የፈረንሳይ ሊዮን የበረራ አገልግሎት አፍሪካን ከዓለም ለማገናኘት በሚደረገው ጉዞ ቁልፍ ምዕራፍ ነው
Jul 1, 2026 1110
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ አየር መንገድ የፈረንሳይ ሊዮን የበረራ አገልግሎት አፍሪካን ከዓለም ለማገናኘት በሚደረገው ጉዞ በቁልፍ ምዕራፍነት እንደሚወሰድ የአየር መንገድ ግሩፑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን አዲስ የመንገደኞች በረራ አገልግሎትን አስጀምሯል። የአየር መንገድ ግሩፑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በዚሁ ወቅት፤ የፈረንሳይ የኢኮኖሚ፣ የባህልና የፈጠራ ብልፅግና ማዕከሏ ሊዮን የሚደረገው በረራ የተደራሽነት አድማስን ያሰፋል ብለዋል። ወደ ሊዮን ከተማ የሚደርገው በረራም የአውሮፓ መዳረሻውን ወደ 23ኛ በማሳደግ የፈረንሳይ ከተሞች ከአፍሪካ ጋር በማገናኘት ስኬታማ ሥራ እየተሰራ መሆኑን እንደሚያሳይ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንድ በፈረንሳይና የአውሮፓ ከተሞች የሚያደርገው የበረራ አገልግሎትም የኢትዮ-አውሮፓን ግንኙነት በማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። አየር መንገዱ ለደንበኞቹ በሚያቀርባቸው ጥራትና ብቃት ያላቸው የበረራ አገልግሎቶችም ዓለም አቀፍ የአቭዬሽን ኢንዱስትሪ ስመጥሩነቱን በተግባር እያስመሰከረ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በሚቀጥለው በጀት ዓመትም አምስት አዳዲስ የበረራ አገልግሎትን በማስጀመር ኢትዮጵያና አፍሪካን በዓለም የንግድ፣ ቱሪዝምና ኢንቨስትመንት ዘርፍ የማስተሳሰር ሚናውን እንደሚወጣ አረጋግጠዋል። አየር መንገዱ የበረራ አገልግሎት ጥራትን ለማላቅም ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በላቀ ቴክኖሎጂዎችና በደንበኛ ተኮር አገልግሎት ላይ ሰፊ ኢንቨስትመንት እያደረገ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ወደ ፈረንሳይ ሊዮን ለሚደረገው የበረራ አገልግሎት መሳካት ድጋፍና ትብብር ላደረጉ ባለድርሻ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል። በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ በበኩላቸው፤ አየር መንገዱ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን ያስጀመረው የበረራ አገልግሎት የሀገራቱን ሁለንተናዊ ግንኙነት ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። በተለይም የኢትዮ-ፈረንሳይን ጠንካራ የዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነት በህዝብ ለህዝብ ትስስር፣ በንግድና ኢንቨስትመንት ለማጠናከር እንደሚረዳ አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀመረ
Jul 1, 2026 821
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው፣ በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ እንዲሁም የአየር መንገዱ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ታድመዋል። የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በረራው የሀገራቱን ግንኙነት የሚያጎለብት ነው። በኢትዮጵያና በፈረንሳይ መካከል ያለውን የንግድ፣ ቱሪዝም እና የባህል ልውውጥ የሚያሳድግ መሆኑንም ጠቁመዋል። አየር መንገዱ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን የሚያደርገው በረራ በአውሮፓ 23ኛ መዳረሻው መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ በበኩላቸው፤ አየር መንገዱ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን ያስጀመረው በረራ የሀገራቱን የንግድና ቱሪዝም ግንኙነት በማሳደግ ረገድ ትልቅ ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑን ገልጸዋል። ሊዮን የፈረንሳይ ሁለተኛዋ የኢኮኖሚ ማእከል መሆኗን ጠቅሰዋል።
የሀዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማት ከሐይቁ የተፈጥሮ ውበት ጋር ተሰናስሎ በልዩ ዲዛይን በላቀ ጥራት እየተገነባ ነው
Jul 1, 2026 574
ሀዋሳ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):-የሀዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማት ከሐይቁ የተፈጥሮ ውበት ጋር ተሰናስሎ በልዩ ዲዛይን በላቀ ጥራት እየተገነባ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለጹ። የከተማዋ ነዋሪዎች በበኩላቸው ለከተማዋ የኮሪደርና የሐይቅ ዳርቻ ልማት ሥራዎች የሚጠበቅባቸውን በመወጣት ታሪካዊ አሻራቸውን እንደሚያሳርፉ ገልጸዋል። ሀገራዊ የኮሪደር ልማት ኢኒሺዬቲቭ መተግበር ከተጀመረ በኋላ ከተሞች ውብ ገፅታና ዘመናዊነትን ከመላበስ ባለፈ ለኑሮና ለንግድ እንቅስቃሴ ምቹ እየሆኑ ይገኛሉ፡፡ በሃዋሳ ከተማ ደግሞ ልማቱ ከተማዋ የቱሪስት መዳረሻነቷ ከፍ እንዲል፣ ለኑሮም ምቹ እንድትሆንና ውበቷም ይበልጥ እንዲጎላ እያደረጋት ነው። በቅርቡም ከኮሪደር ልማቱ በተጨማሪ የተፈጥሮ ጸጋዎቿ እንዲገለጡ የሚያደርግና ከኮሪደር ጋር የተሰናሰለ የሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት በይፋ ተጀምሯል፡፡ ፕሮጀክቱን በማስመልከት ኢዜአ ያነጋገራቸው የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ እንዳሉት፤ የሀዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማት ከሐይቁ የተፈጥሮ ውበት ጋር ተሰናስሎ በልዩ ዲዛይን በላቀ ጥራት እየተከናወነ ነው። የሐይቅ ዳርቻ ልማቱ የከተማዋን የኮንፈረንስ ማዕከልነት እንዲሁም የጎብኚዎቿን የቆይታ ጊዜ እንደሚያራዝመው አንስተዋል፡፡ ፕሮጀክቱ የማህበረሰቡ አሻራ በጉልህ እንዲያርፍ ታስቦ መጀመሩን የገለጹት ከንቲባው 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በጀት እንደተያዘለትና ህብረተሰቡም በአቅሙ አስተዋጽኦ በማድረግ የድርሻውን እንዲወጣ አመልክተዋል። እንደ ከንቲባ ጥራቱ ገለጻ፤ በከተማዋ በ2ኛ እና በ3ኛ ዙር 8 ነጥብ 9 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የኮሪደር ልማት ሥራ ተከናውኗል። ልማቱም የብስክሌት፣ የሞተር ብስክሌትና የመኪና ማቆሚያዎች፣ የታክሲ መጫኛና ማውረጃ፣ የሕፃናት መጫወቻዎችንና የወጣቶች የስፖርት ማዘውተሪያዎች አካቶ የተከናወነ መሆኑንም አመልክተዋል። በአሁን ወቅት 4 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው አራተኛው ዙር የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ ልማቱም ከሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ጋር መሰናሰሉን አመልክተዋል። የሀዋሳ ከተማ ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ በከተማዋ እየተከናወኑ ባሉ የኮሪደርና የሐይቅ ዳርቻ ልማት ሥራዎች የሚጠበቅባቸውን በመወጣት ታሪካዊ አሻራቸውን እንደሚያሳርፉ አረጋግጠዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል ወይዘሮ ያምሮት ኃይሌ የኮሪደር ልማቱ ሀዋሳ ድሮ ከነበራት ውበት በላይ እንዳደመቃትና ተወዳዳሪ እንዳደረጋት ተናግረዋል። በሆቴል ሥራ ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ለገሰ ላሚሶ በበኩላቸው፤ በከተማዋ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ሥራ በተለይ የሆቴል ዘርፉ እንዲነቃቃ የጎላ ሚና እንዳለው ተናግረዋል። ወደ ሀዋሳ የሚመጡ እንግዶችን በላቀ መስተንግዶ ተቀብለው ለማስተናገድ ይበልጥ መነቃቃታቸውን ገልጸው፣ የተጀመረው የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ተጠናቆ ከተማዋ ይበልጥ እንድታድግ የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስታውቀዋል፡፡
በኢትዮጵያ በቱሪዝም ልማትና ቅርስ ጥበቃ የተከናወኑ ተግባራት አስደናቂ ውጤት የተመዘገበባቸው ናቸው
Jul 1, 2026 373
ወላይታ ሶዶ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በቱሪዝም ልማትና ቅርስ ጥበቃ ረገድ የተከናወኑ ተግባራት አስደናቂ ውጤት የተመዘገበባቸው መሆኑን ምሁራን ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል በሰጡት ማብራሪያ በዘርፉ ልማት የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን በስፋት አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በዝርዝር አስቀምጠዋል። በተለይም የገበታ ፕሮጀክቶች ግንባታ፣ የከተሞች ኮሪደር ልማትና የቆዩ ቅርሶች እድሳት ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ትልቅ አቅም እንደሆኑ አንስተዋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ካነጋገራቸው የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን መካከል በዩኒቨርሲቲው የጋዜጠኝነትና የተግባቦት ትምህርት መምህርና ተመራማሪ ተሻለ ተገኔ (ዶ/ር)፤ በኢትዮጵያ በቱሪዝም ዘርፍ ላይ ኢንቨስት ማድረግ የዘርፉን ተወዳዳሪነትና ተመራጭነቷን ያሳድጋል ብለዋል። ለዚህም መንግስት ተግባራዊ ባደረጋቸው ገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሃገርና ገበታ ለትውልድን ጨምሮ በወንዝ ዳርቻ ልማቶች ያከናወናቸው ተግባራት የዘርፉን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ፋይዳ እንደሚያጎሉ አንስተዋል፡፡ የልማት ሥራዎቹ የሀገርን ገጽታ ከመገንባት ባለፈ የሥራ ዕድልን ለማስፋት እና የውጭና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎችን ቁጥር በመጨመር በኩል የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ጠቁመዋል። የለውጡ መንግስት ዘርፉን በፖሊሲ በመምራት የቱሪስት መዳረሻ ስፍራዎች ልማት፣ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ማጠናከር እንዲሁም የሰው ሀይል ማፍራት ላይ ትኩረት ማድረጉን ጠቁመዋል። ይህም የቱሪዝም ዘርፉን እያነቃቃው መሆኑን ገልጸው፣ የዘርፉን ጠቀሜታ ይበልጥ ለማሳደግ ምሁራን በጥናትና ምርምር የመደገፍ ሃላፊነታችንን ማጠናከር ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡ በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ዜጋና ሥነ ምግባር ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ጣሰው ታደሰ በበኩላቸው እንዳሉት፣ ከለውጡ በፊት በሀገር አቀፍ ደረጃ ጥቂት ታሪካዊ መዳረሻዎች ብቻ ቢኖሩም በበቂ ሁኔታ ሳይለሙ ቆይተዋል። ይህንን ለመቀየርና ቱሪዝም በሀገር ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ላይ ያለውን አበርክቶ ለማሳደግ የለውጡ መንግስት ዘርፉን በፖሊሲ ማሻሻያ ማገዙና መምራቱ የላቁ ውጤቶች እንዲመዘገቡ አድርጓል ብለዋል። በእዚህም በርካታ የሀገሪቱ ከተሞች የኮንፍረንስ ቱሪዝም ማዕከል እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቁመዋል። የቱሪዝም ዘርፉን ከቴክኖሎጂ ጋር በማስተሳሰር መዳረሻዎች ይበልጥ እንዲተዋወቁ የተጀመሩ ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸውም አክለዋል፡፡
በዞኑ በበጋ መስኖ ልማት የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል
Jul 1, 2026 203
ደብረ ማርቆስ ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):- በምስራቅ ጎጃም ዞን የበጋ መስኖ ልማት ስራን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉን የዞን ግብርና መምሪያ ገለጸ። የዞኑ ግብርና መምሪያ የመስኖ ልማት ባለሙያ አቶ ካሳሁን ዘለቀ ለኢዜአ እንደገለጹት፤የበጋ መስኖ ልማት ስራ አርሶ አደሩ የዝናብ ወቅትን ጠብቆ ከማምረት እንዲወጣ በማድረግ ለውጥ ለማስመዝገብ አስችሏል። አርሶ አደሩ በበጋ መስኖ ልማት ስራ በስፋት እንዲሰማራ የተከናወነውን የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራ ጨምሮ በወቅቱ ግብአት እንዲቀርብለት መደረጉም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ ያስቻለ መሆኑን አንስተዋል። ለአብነትም በዘንድሮው በጋ ወራት ከ 50 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን መሬትን በመስኖ በማልማት ከ4 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን ጠቁመዋል። የመስኖ ልማቱ ይበልጥ ምርታማነትን ለማሳደግ እንዲያስችልም ከ67 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ መዋሉን አስረድተዋል። በመስኖ ልማት ስራው 100 ሺህ አርሶ አደሮች የተሳተፉ ሲሆን የተገኘው ምርት ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከ1 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ብልጫ አለው ብለዋል። ለተገኘው ስኬት የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ጨምሮ የባለሙያዎች የተጠናከረ ድጋፍ ተጠቃሽ ነው ብለዋል። በበጋው ወራት መስኖ ልማት በመሳተፍ ተጠቃሚ ከሆኑ አርሶ አደሮች መካከል የማቻከል ወረዳ የየውላ ቀበሌ አርሶ አደር አዲሱ ይዘንጋው ፤ ባላቸው አንድ ሄክታር መሬት ላይ ስንዴ እና በቆሎ በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የገለጹት። የመስኖ ልማት ስራው ከዝናብ ጥገኝነት በመውጣት እና በሁለት ዙር በማምረት ከቤት ፍጆታ አልፎ ለገበያ የሚቀርብ ምርት እንዲያገኙ በማድረግ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው አስረድተዋል። ከባለሙያዎች ያገኙትን ግንዛቤና ግብአት በመጠቀም በመስኖ ልማት ስራ በመሰማራት በግማሽ ሄክታር መሬት ላይ የጓያና የጓሮ አትክልትን አልምተው ተጠቃሚ መሆናቸውን ያነሱት ደግሞ በዞኑ የአነደድ ወረዳ የወጀል ቀበሌ አርሶ አደር እንዳላማው ጫኔ ናቸው። የበጋ መስኖ ስራ የተለያዩ ሰብሎችን በማልማትና በማስፋፋት ኑሮዋቸውን ለመቀየር እንዳስቻላቸውም ተናግረዋል።
በክልሉ ያሉ ጸጋዎችን መሰረት ያደረገው ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ወጣቶችን ተጠቃሚ አድርጓል
Jul 1, 2026 339
ሀዋሳ፤ ሰኔ 24/2018(ኢዜአ)፡-በሲዳማ ክልል ያሉ እምቅ ጸጋዎች በመለየት የተከናወኑ ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራዎች ተጠቃሚ እንዳደረጓቸው ወጣቶች ገለጹ። የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ በበኩሉ ጸጋዎችን በመለየትና ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከር የወጣቱን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን አስታውቋል። በክልሉ በአለታ ጩኮ ወረዳ ጭጮ ወያማ ቀበሌ በሥራ ዕድል ፈጠራ ተጠቃሚ የሆኑ ወጣቶች የሥራ እንቅስቃሴ ላይ ምልከታ ተደርጓል። በቀበሌው ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የተመረቁ ከ200 በላይ ወጣቶች ተደራጅተው ከ62 ሄክታር በላይ መሬት ላይ በቆሎ በኩታ ገጠም እያለሙ መሆናቸውን ተናግረዋል። አስተያየቱን ለኢዜአ የሰጠው ወጣት ፊልጶስ ይስሐቅ፣ መንግስት ከዩኒቨርሲቲ ለተመረቁ ወጣቶች የወል መሬት በማመቻቸት እና ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በማቅረብ በግብርና ልማት እንዲሰማሩ ማድረጉን ተናግሯል። በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል ደስተኛ መሆኑን ገልጾ፣ በመጀመሪያ ዙር ያለሙት የበቆሎ ሰብል በጥሩ ቁመና ላይይገኛል ብሏል። ሌላኛው የይርጋለም ከተማ ነዋሪ ወጣት አገኘሁ ከቦ በበኩሉ እሱን ጨምሮ 100 ወጣቶች በስምንት ማህበራት ተደራጅተው የአቮካዶ ችግኝ በማፍላት ሥራ መሰማራታቸውን ተናግሯል ። በአካባቢው የአቮካዶ ዘይት አምራች ኩባንያዎች መኖር እና ለአረንጓዴ አሻራ ልማት የተሰጠ ትኩረት ውጤታማ እንደሚያደርጋቸው የአዋጭነት ጥናት መስራታቸውን ጠቅሶ፤ ወደስራ ሲገቡም የመነሻ ካፒታል፣ የመስሪያ ቦታ እና የተሻሻለ የአቮካዶ ዘር እንዳቀረበላቸው ገልጿል። በአሁኑ ወቅትም 40 ሺህ የተሻሻሉ የአቮካዶ ችግኞችን አፍልተው ለገበያ ለማቅረብ መዘጋጀታቸውን ገልጸው፣በወቅቱ ገበያ አንድ ችግኝ እስከ 150 ብር እንደሚሸጥ ተናግረዋል። በሀዋሳ ከተማ በኮሪደር ልማት ሥራ በአረንጓዴ ልማት ዘርፍ ተደራጅተው ወደሥራ እንደገቡ የተናገረው ወጣት ምንተስኖት ደሳለኝ በበኩሉ በተፈጠረው የሥራ ዕድል ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግሯል። የሲዳማ ክልል ስራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ከፍያለሁ ከበደ በበኩላቸው እንዳሉት በክልሉ ያሉ የሥራ ዕድል አማራጮችን በመጠቀም በርካታ ወጣቶችን ወደሥራ ለማስገባት ተችሏል። ለወጣቱ በሥራ ፈጠራ ላይ አጫጭር ስልጠናዎችን በመስጠት፣ ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከር፣ የመስሪያና መሸጫ ቦታ እንዲሁም መነሻ ካፒታል በማመቻቸት የሚደረጉ ክትትልና ድጋፎች ውጤት ማምጣታቸን አስረድተዋል ። በዚህም በበጀት ዓመቱ ከ564 ሚሊዮን ብር በላይ የገንዘብ ብድርና 341 ሼዶች መቅረባቸውን ጠቅሰው ሁሉም ተቋማት በተቀናጀ መልኩ ለወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራ የሰጡት ትኩረት ውጤት እያመጣ ነው ብለዋል ። የወጣቱን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማስፋት በተደረገ ጥረት ወጣቱ ተቀጣሪ ከመሆን ይልቅ ስራን መፍጠር ላይ እያተኮረ መምጣቱን ተናግረው፣ በዘርፉ የተገኘውን ውጤት የማስፋት ሥራ ይጠናከራል ብለዋል።
በወላይታ ዞን በዲጂታል ቴክኖሎጂ በመታገዝ ከ5 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰበሰበ
Jul 1, 2026 263
ወላይታ ሶዶ ፤ ሰኔ 24/2018(ኢዜአ)፦ በወላይታ ዞን በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ የግብር አሰባሰብ ሂደትን በመጠቀም ከ5 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን የዞኑ ገቢዎች መምሪያ አስታወቀ። የዞኑ ገቢዎች መምሪያ ከዞኑ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ጋር በመተባበር የ2018 ዓ/ም የግብር ዘመን የታክስ አሰባሰብና የ2019 የንግድ ፈቃድ ዕድሳት ንቅናቄ መድረክ በወላይታ ሶዶ ከተማ በመካሄድ ላይ ነው። በመድረኩ የዞኑ ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ዘካሪያስ ታደሰ በዘንድሮ በጀት ዓመት 5 ነጥብ 51 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ እስከ ሰኔ 23/2018 ዓ.ም ድረስ 5 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር መሰብሰብ ተችሏል ብለዋል። ይህም አፈፃፀሙን 95 በመቶ ማድረሱን አንስተው ተግባሩ እስከ ሰኔ 30 ድረስ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ የገቢ አሰባሰቡ ዲጂታል የተደገፈው አሰራርና የባለሙያዎች ቁርጠኝነት የተሻለ ገቢ እንዲሰበሰብ ማገዙን አስረድተዋል። ከመረጃ አያያዝና ትንተና ጀምሮ በገቢ አሰባሰብ ሂደት የሚስተዋሉ ችግሮችን በመፍታት የተቀመጡ ግቦችን ለማሳካት በጋራ ተቀናጅቶ መስራት እንደሚገባም አመልክተዋል። ከሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ/ም ጀምሮ የግብር ዘመኑ የታክስ አሰባሰብና የንግድ ፈቃድ ዕድሳት እንደሚጀመርም ገልጸዋል። የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ተስፋሁን ታዴዎስ በበኩላቸው ዞኑ በተለያዩ ዘርፎች የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ ለመሰብሰብ እየተሰራ ነው ብለዋል። ውጤቱ ሁሉም ባለድርሻ አካላትና ባለሙያዎች ተቀናጅተው በመስራታቸው የመጣ መሆኑን በማንሳት ቀጣይ የህዝቡን አዳጊ የልማት ፍላጎት ለማሟላት የገቢ አሰባሰብ ስርዓቱን በማዘመን አጠናክሮ ማስቀጠል ያስፈልጋል ብለዋል። የዞኑ ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ ለመሰብሰብ እንቅፋት የሆኑ እንደ ህገወጥ ንግድና ያለደረሰኝ የሚደረገውን ግብይት በቁርጠኝነት መቆጣጠር እንደሚገባም አሳስበዋል። የንቅናቄ መድረኩ ዓላማም የተሻለ ገቢ ለመሰብሰብ እና የንግድ ስራ ፈቃድ ዕድሳት ተግባርን በተቀመጠው የጊዜ ገደብ ለማጠናቀቅ የሚያስችል ምክክር ለማድረግ መሆኑንም አስረድተዋል። በመድረኩም የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር የመንግስት የስራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
ትላንትን ከዛሬና ከነገ ጋር ማስተሳሰር - የመደመር መንግስት እይታ በቱሪዝም
Jul 1, 2026 708
ቱሪዝም ልዩ ትኩረት የተሰጠው በመላው ዓለም ከፍተኛ ገንዘብ የሚንቀሳቀስበት ዘርፍ ነው። ይህ ዘርፍ በአህጉራችን አፍሪካም ከፍተኛ ገቢ የሚያገኙበት ሃገራት እንዳሉ ይታወቃል። ቱሪዝም ከገቢነት ከኢኮኖሚያዊ እቅምነት ባለፈ ትውልድን ያስተሳስራል ብሄራዊ ትርክትን ለመገንባትም ያግዛል ። ትላንትን ከዛሬ ዛሬንም ከነገ ጋር የሚያስተሳስር ነው። “ሀገራችን ከቱሪዝም ልታገኛቸው የምትችላቸውን ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና አካባቢያዊ ጥቅሞች ሁሉ ከቀረው ዓለም ጋር ተወዳድራ እንድታገኝ፣ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ጎብኚ ወደ ሀገራችን መሳብ አለብን። ለዚህም የተለያዩ ስልታዊ መላዎች ነድፈን እየተንቀሳቀስን እንገኛለን (የመደመር መንግሥት 273)። የቱሪዝም ኢንዱስትሪ የለውጡ መንግሥት እመርታዎችን ካስመዘገበባቸው ዘርፎች አንዱ ነው። መንግስት ከአምሥቱ የትኩረት መስኮች አንዱ አንድርጎም በጥናት፣ አካባቢያዊ ፀጋን ዐውቆና ለይቶ በተደመረ ዐቅም ባከናወናቸው ሥራዎች በገበታ ለሸገር፣ በገበታ ለሀገር፣ በገበታ ለትውልድ፣ በኮሪደር ልማት፣ በወንዝ እና የወንዝ ዳርቻዎች ልማት እሠየው ያሰኙ ተግባራት አከናውኗል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው ከእንጦጦ - ቀበና የተከናወነው የወንዝና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክትም ለጎብኚም ለነዋሪም ምቹ ከባቢን በመፍጠር ረገድ እየተደረገ ያለውን ትጋት ያስረዳል። ምረቃውን ተከትሎ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ባጋራው መረጃ፤ “መቆሸሽ እኛ አይገባንም፣ መጠልሸት እኛ አይገባንም፣ ማነስ እኛ አይገባንም! ሠርተን እንደምንችል ማሳየት ያስፈልጋል” ሲል የሥራውን ማራኪነትና ውበት ገልጿል። ጠቅላይ ሚኒስትሩም በዚሁ ወቅት፤ የተሰጠንን ሕዝባዊ አደራ በታማኝነት፣ በጽኑ ትጋት እና በቅንነት በመፈጸም የዜጎቻችንን የኑሮ ጥራት ለማሻሻልና መሠረታዊ ለውጥ ለማምጣት የጀመርነውን ጉዞ አበክረን እንቀጥላለን ሲሉ በቀጣይ ካለፈው የበለጠ እንደሚሠራ አመላክተዋል። ገንዘብን፣ ዕውቀትን፣ ጉልበትን፣ ሐሳብን፣ የአመራር ብቃትን ስንደምር የሚከሰተው ነገር እንደዚህ ያለው ውበት ይሆናል ሲሉም አስገንዝበዋል። በመደመር መንግሥት መጽሐፋቸው (ገጽ 256) ላይም፤ “የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ሀገራት በዘመናቸው ሁሉ የሠሩትንና ተፈጥሮ ያደለቻቸውን መልካም ገጽታ በኩራት ለዓለም የሚያስተዋውቁበት፣ ‘ሀገሬ ይሄንን ትመስላለች’ የሚሉበት መድረክ ነው። ሀገርን በሚያኮራና ለሌሎች ለመጋበዝ በማያሳፍር መልኩ መገንባት፣ ለቱሪዝም ኢንዱስትሪ መሠረቱ ነው።” ያሉትም የበለጸገች ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ በቁጭት መነሳታቸውን ይገልጻል። ነገን ዛሬ እየሠራች ያለችው ኢትዮጵያ ካላት ላይ ሳትነፍግ የገንዘብም ሆነ የሰው ኃብቷን ቱሪዝም ላይ ስታውል፤ አንድም የኢንዱስትሪውን ዐዋጭነት ብሎም የዜጎቿን በየዘርፉ ዘላቂ ተጠቃሚነት በመገንዘብ ነው። እዚህ ላይ ለሀገር ገቢ በማስገኘት እና የሥራ ዕድል በመፍጠር ዘርፉ የሚያበረክተውን ጥቅም ማጤን ይገባል። በአዲስ አበባ ከተከናወኑ ቁልፍ የቱሪዝም ልማቶች መከካከል፤ የመስቀል ዐደባባይ ቅርስን ማንበርና ማዘመን፣ ከአዲስ አበባ ልማት ጋር ተሣሥሮ የተገነባው የዓድዋ ድል መታሰቢያ፣ በአዲስ መልክ የታደሠው ብሔራዊ ቤተ-መንግሥት፣ የአምሥቱ ዕውቀት ተኮር ማዕከላት (አብርኾት ቤተ-መጻሕፍት፣ ሳይንስ ሙዝየም፣ የሀገር በቀል ዕጽዋት ማሳያ፣ የአንድነት ቤተ-መዛግብት እና የማዕድን ሙዝየም) ግንባታ፣ የአዲስ አበባ ኮንቬንሽን ማዕከል እና ሌሎችም ይገኙበታል። በሌላ በኩል ደግሞ ጎብኚዎች የሚያርፉበት ሎጂና ሆቴሎች ግንባታም በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። ገበታ ለሸገር ብሎ ከአዲስ አበባ የተነሳው የቱሪዝም ልማት በገበታ ለሀገርና ገበታ ለትውልድ ወደ ክልሎች ተስፋፍቶ ደረጃቸውን የጠበቁ ሎጂዎች እንዲገነቡ አስችሏል። የተገነቡት ሎጂዎች ደግሞ ለጎብኚዎቹ ምቾትን የሚያስጠብቁ መሠረተ-ልማቶችን ስበዋል። በርካታ ጎብኚ መሳብና ገቢን ማሳደግ፣ በጎ ገጽታን መሸጥ፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር፣ የበለጸገች ኢትዮጵያ ዕውን ማድረግ እየተከናወኑ ላሉ ተግባራት ሁሉ ግቦች ናቸው። መንግሥት ዕምቅ የጎብኚዎች መስኅብ ዐቅም የሆኑና አቧራ ለብሰው የተደበቁትን ፀጋዎች ውበታቸውን ገላልጦ እያሳዬ ያለውም ለዚህ ነው። ቱሪዝም በቀጥታ ዜጎች (ሰዎች) የሚጠቀሙበት ኢንዱስትሪ ነው። ለዚህ ደግሞ ሰዎች ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠርና መጠበቅ ይኖርባቸዋል።መሠረተ-ልማቶችን በመጠበቅ እንዲሁም ከመንግሥት ጎን በመሆን በሚፈለጉበት ሁሉ ንቁ ተሳትፎ በማድረግም ይጠበቅባቸዋል።
በአርብቶ አደሩ አካባቢ ተግባራዊ የተደረገው የእንስሳት ኢንሹራንስ ውጤት እያመጣ ነው
Jul 1, 2026 345
ሮቤ፣ ሰኔ 24/2018 (ኢዜአ)፡- የኦሮሚያ ክልል የአርብቶ አደሩን ማኅበረሰብ ኑሮ ለማሻሻልና የእንስሳት ሀብቱን ከአደጋ ለመጠበቅ ተግባራዊ ያደረገው የእንሰሳት ኢንሹራንስ ውጤት እያመጣ መሆኑን የክልሉ መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ገለጸ። የእንስሳት ኢንሹራንሱ የአርብቶ አደሩን ማኅበረሰብ የአደጋ ስጋት ተጋላጭነት ለመቀነስና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቱን ይበልጥ ለማሳደግ ጉልህ ድርሻ እንዳለው ተመልክቷል። የቢሮው ምክትል ኃላፊና የአርብቶ አደር ልማት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ሮባ ቱርቼ በተለይ ለኢዜአ እንዳሉት፣ በክልሉ የአርብቶ አደሩን ማኅበረሰብ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል። በተለይ አርብቶ አደሩ የድርቅ ተጋላጭነቱን እንዲቀንስና ከእንስሳት ሀብቱ ይበልጥ ተጠቃሚ እንዲሆን የሚያግዙ አሠራሮች መዘርጋታቸውን አመልክተዋል። ከዚህ ውስጥ የእንስሳት ኢንሹራንስ ፖሊሲ አንዱ መሆኑን ጠቅሰው፤ ኢንሹራንሱ የአርብቶ አደሩን ማኅበረሰብ የድርቅ ተጋላጭነት ለመቀነስ እና ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ እያገዘ መምጣቱን ተናግረዋል። የአደጋ ስጋት ቅነሳ ፕሮጀክቱ በክልሉ ላለፉት ሁለት ዓመታት ተግባራዊ ሲደረግ መቆየቱንም ገልጸዋል። በእንስሳት ኢንሹራንሱም መኖ፣ ውሃና መድኃኒት እንደሚገዛ የጠቀሱት ኃላፊው፤ ድርቅ ሲያጋጥም ደግሞ እንስሳቱ ሳይጎዱ ወደ ጥሬ ገንዘብ የሚለወጡበት አሠራር ጭምር የሚተገበርበት መሆኑን ተናግረዋል። ለአብነትም በበጀት ዓመቱ ከ22 ሺህ ለሚበልጡ የኢንሹራንስ አባል አርብቶ አደሮች ከ413 ሚሊዮን ብር በላይ ለመኖ እና ውሃ አቅርቦት እንዲሁም ለእንስሳት ጤና መጠበቂያ የሚሆን ክፍያ መፈጸሙን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት ሁለት ዓመታት አነስተኛ የዝናብ እጥረት በተከሰተባቸው የአርብቶ አደር አካባቢዎች የጎላ ችግር ሳያጋጥም፣ በተፈጠረው አካባቢያዊ አቅም ድርቁን መቋቋም መቻሉ የዚሁ ጥረት ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል። ከኢንሹራንሱ ጎን ለጎን የሚስተዋለውን የእንስሳት መኖ እጥረት ለመቅረፍ፣ በተለያዩ ዞኖች ለግጦሽ ከተለዩ ከ3 ሚሊዮን ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ከ409 ሺህ 900 ቶን በላይ የመኖ ሳር በማምረት ማከማቸት መቻሉን ገልጸዋል። የእንስሳት መኖን ለማከማቸት የሚያግዙ ከ17 የሚበልጡ ትላልቅ የማከማቻ ማዕከላት ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውንም አክለዋል። የአርብቶ አደሩን የእንስሳት ገበያ በየአካባቢው ተደራሽ በማድረግና የግብይት ሰንሰለቱን ለማሳለጥ የተገነቡት 20 የሚሆኑ ማዕከላት፣ አርብቶ አደሩ ከገዢው ጋር በቀጥታ ተገናኝቶ እንዲገበያይ እያደረጉ መሆኑን አቶ ሮባ አስታውሰዋል። የክልሉ መንግሥት ይህንን የእንስሳት ኢንሹራንስ ይበልጥ ተደራሽ በማድረግ፣ የአርብቶ አደሩን የአኗኗር ዘይቤ ለማዘመንና አካባቢያዊ ተጽዕኖዎችን የመቋቋም አቅምን ለመገንባት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አመልክተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር በሚል ርዕሰ ጉዳይ ከኤን ቢ ሲ ጋር ባደረጉት ቆይታ ካነሷቸው ዋና ዋና ነጥቦች መካከል፦
Jul 1, 2026 233
ከቱሪዝም መሠረተ-ልማት ጋር በተያያዘ አበረታች ሥራዎች ተሠርተዋል። በተለይም በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገር እና ገበታ ለትውልድ ስኬታማ ተግባራት ተከናውነዋል፤ አሁንም እየተከናወኑ ያሉና በቅርቡ የሚመረቁ አሉ። ባለፉት ጥቂት ወራት ብቻ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰባት የአውሮፕላን ማረፊያዎችን አስመርቀናል። በተጨማሪም በርካታ መንገዶች ተገንብተዋል። ይህም ለቱሪዝሙ ከፍተኛ መነቃቃት ይፈጥራል። የኢትዮጵያ የግሉ ዘርፍ (ፕራይቬት ሴክተር) በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገር እና ገበታ ለትውልድ ፕሮጀክቶች ግብ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ አሁን ለመጣው የቱሪዝም መነቃቃትና ሥራ የማይተካ ሚና ተጫውቷል። ቱሪዝም ቅርስ ብቻ አይደለም፤ ቅርስ ስላለ በቀጥታ ቱሪዝም ይሳባል ማለት አይደለም። ቱሪዝም የተፈጥሮ ሀብት ብቻም አይደለም። ቱሪዝም ሸመታ ከሌለው በሴክተሩ የገንዘብ ልውውጦች (ትራንዛክሽን) ከሌለው የቱሪዝም ኢኮኖሚ ሊባል አይችልም። ቱሪዝም በአጭሩ ሊጎበኘን የመጣ ሰው ልቡ ተደስቶ፤ ኪሱ ተራቁቶ መሄድ አለበት ማለት ነው። ከፕሮሞሽን አንጻር ብዙ ሥራ ይጠበቅብናል። ብዙ የማስተዋወቅ ሥራ እንደሚቀረን እኛም እናውቃለን፤ ወዳጆቻችንም ይነግሩናል። እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ኢትዮጵያን አስውቦ፣ አሳምሮ፣ አልቆ የመሥራት ብቻ ሳይሆን የመግለጥ ኃላፊነት አለበት። ሀገራችንን ማስተዋወቁን በተቀናጀ መንገድ ስንሠራ የምናገኘውም ጥቅም በዚያው ልክ እያደገ ይሄዳል። በሚሠሩት ሥራዎች የኢትዮጵያ ሕዝብ ቅርስ ይጠፋብኛል ብሎ ይሰጋል ብዬ አላምንም። እንደዛ ዓይነት ስጋት አላይም። በዚህ ዓመት 10 ነጥብ 2 ጂ ዲ ፒ ዕድገት እንጠብቃለን። ይህ ዕድገት በኢትዮጵያ ብቻ እንጅ በድፍን አፍሪካ የለም። በዚህ ዓመት ከ10 ነጥብ 8 እስከ 11 ቢሊየን ዶላር ኤክስፖርት እናደርጋለን። ይህ ከሁለት/ሦስት ዓመት በፊት ሦስት ቢሊየን ዶላር የነበረ ነው። በዚህ ዓመት ከ1 ነጥብ 4 ሚሊየን በላይ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች ኢትዮጵያን ጎብኚተዋል። ይህ ቁጥር ከካች አምናው አንጻር የ300 ሺህ እንዲሁም ካለፈው ዓመት አንጻር የ100 ሺህ ቱሪስቶች ቁጥር ጭማሪ አለው። ከውጭ ሀገራት ጎብኚዎችም (ማይንስ ተጨምሮ) ዘንድሮ ከ 5 ነጥብ 4 ቢሊየን ዶላር በላይ ገቢ ተገኝቷል። በተመሳሳይ 50 ነጥብ 16 ሚሊየን ኢትዮጵያውያን ደግሞ የተለያዩ የሀገራቸውን ክፍል ጎብኝተዋል። ይህ አሃዝ ከታች ዓምናው አንጻር በ9 ነጥብ 4 ሚሊየን እንዲሁም ካለፈው ዓመት አንጻር በ1 ነጥብ 8 ሚሊየን ብልጫ አለው። ከሀገር ውስጥ ጎብኚዎች ከ79 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ ተገኝቷል። በዚህ ዓመት 204 ዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶች ተካሂደዋል። ይህ አሃዝ ካለፈው ዓመት አንጻር የ50 ኮንፈረንሶች ብልጫ አለው። ከካች አምና አንጻር የ166 ኮንፈረንሶች ብልጫ አለው። በዚህ ዓመት ለማይንስ (ኮንፈረንስ) ቱሪዝም ብቻ ከ166 ሺህ በላይ ተሳታፊዎች ወደ ኢትዮጵያ መጥተዋል። ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት 1 ነጥብ 5 ትሪሊየን ብር ትሰበስባለች። ከለውጡ በፊት 200/300 ሺህ ብር ነበር ዓመታዊ ገቢ የመሰብሰብ ዐቅም።
የብዝሃ ዘርፍ ሪፎርሙ የቱሪዝሙን የኢኮኖሚ አበርክቶ አሳድጓል -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jul 1, 2026 1025
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 23/2018 (ኢዜአ)፦ የብዝሃ ዘርፍ ሪፎርሙ ለቱሪዝም መስክ የኢኮኖሚ አበርክቶ ማደግ ትልቅ ሚና መጫወቱን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከኤንቢሲ ኢትዮጵያ ጋር ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር በሚል ርዕስ ቆይታ አድርገዋል። መንግስታቸው የጀመረው የብዙሃ-ዘርፍ (Multi-sectoral) የኢኮኖሚ ሪፎርም በአሁኑ ወቅት በአስደናቂ ሁኔታ ውጤት እያስመዘገበ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በግብርናው ዘርፍ በስንዴ፣ በቡና፣ በሩዝ እንዲሁም በፍራፍሬ ልማት የተገኙ ውጤቶች ለሀገር ውስጥ ምርታማነት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ጠቁመዋል። ከዚህም በተጨማሪ እንደ ሌማት ትሩፋት ያሉ ኢኒሼቲቮች፣ የቴክኖሎጂ ሪፎርሞች፣ የመሶብ ፕሮጀክት እና የአምስት ሚሊየን ኮደሮች የስልጠና መርሃ-ግብር ለጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP) እድገት የበኩላቸውን ጉልህ ድርሻ እየተወጡ መሆኑን አስገንዝበዋል። በኢንዱስትሪ እና በማዕድን ዘርፎች የተመዘገቡት ስኬቶችም የኢኮኖሚ ማሻሻያው አካል መሆናቸውን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ሀገሪቱ ከእነዚህ ዘርፎች በርካታ ቢሊየን ዶላሮችን እያገኘች መሆኑን አመልክተዋል። የተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች በየበኩላቸው እያበረከቱት ባለው ሁለንተናዊ ድርሻ ምክንያት የሀገሪቱ ኢኮኖሚ በተከታታይ እያደገ መሆኑን ገልጸው፤ በተያዘው በጀት ዓመት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የ 10 ነጥብ 2 በመቶ እድገት ያስመዘግባል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል። የቱሪዝም ዘርፍን በተመለከተ በዘንድሮው ዓመት ከ1 ነጥብ 4 ሚሊየን በላይ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች ኢትዮጵያን የጎበኙ ሲሆን፤ ይህም ቁጥር ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ100 ሺህ በላይ፣ ከካቻምናው አንጻር ደግሞ የ300 ሺህ የጎብኚዎች ጭማሪ ማሳየቱን አብራርተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም የውጭ ቱሪስት ፍሰቱና የተገኘው ገቢ እያደገ ቢሆንም፤ ገና የሚፈለገው ደረጃ ላይ ባይደርስም የታየው ለውጥ ግን እጅግ ተስፋ ሰጪና በግልጽ የሚታይ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማዕከል በመሆኗ በበጀት ዓመቱ 204 ዓለም አቀፍ ኮንፈረንሶችን እና ታላላቅ ሁነቶችን ማስተናገዷን ገልጸው፤ ይህም ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተሰሚነት ከማሳደጉም በላይ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ስበት ማዕከል እየሆነች መምጣቷን ማረጋገጫ ነው ብለዋል። በሰው ኃይል ልማት፣ በቱሪስቶች ፍሰት፣ በገቢ አሰባሰብ እና በአዋጪነት ረገድ የቱሪዝም ዘርፍ ለመንግስት የሪፎርም ስራዎች ፈጣንና አዎንታዊ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አመልክተዋል። በተለያዩ ጊዜያት ያጋጠሙ ፈተናዎች ቢኖሩም፤ ቱሪዝም ለብሄራዊ ኢኮኖሚው ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝና ዘርፉን እንደ አንዱ የኢኮኖሚ ምሰሶ አድርጎ መምረጥና መዋዕለ ንዋይ ማፍሰሱ ፍጹም ትክክለኛ እርምጃ እንደነበር በተከናወኑት ስኬታማ ስራዎች ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል።
ኢትዮጵያ የብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፍ አቅጣጫን ተግባራዊ በማድረጓ በሁሉም መስክ ፈጣንና ተከታታይነት ያለው ዕድገት ማስመዝገብ ችላለች - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jun 30, 2026 1876
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 23/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ የብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፍ አቅጣጫን ተግባራዊ በማድረጓ በሁሉም መስክ ፈጣንና ተከታታይነት ያለው ዕድገት ማስመዝገብ መቻሏን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያ ከለውጡ ወዲህ ከግብርና መር የኢኮኖሚ አቅጣጫ ወደ ብዝሃ ዘርፍ የኢኮኖሚ አቅጣጫ መሸጋገሯ ይታወሳል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ብዝሃ ዘርፍ የኢኮኖሚ አቅጣጫ መከተል ከጀመረች ወዲህ በሁሉም ዘርፎች የሚያስደንቅ ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል፡፡ በግብርና ዘርፍ በስንዴ፣ በቡና፣ በሩዝ፣ በፍራፍሬ፣ በሌማት ትሩፋት፣ በዶሮና ወተት የተገኙ ውጤቶች አስደናቂ ናቸው ብለዋል፡፡ በቴክኖሎጂ ዘርፍም በ5 ሚሊዮን ኮደርስ፣ በዲጂታል መታወቂያ፣ በሞባይል መኒ፣ በቴሌ ብር አንጸባራቂ ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል፡፡ የኢንዱስትሪ ዘርፍም ለዘመናት ውስን አቅም የነበረው ዘርፍ እንደነበር አውስተው፤ አሁን ላይ ግን እጅግ በተሻለ ሁኔታ እያደገ እንደሚገኝ አንስተዋል፡፡ ከዘርፉ የሚገኙ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ ምንጭ ሆኖ እያገለገለ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ ከ30 እስከ 40 ሚሊዮን ዶላር ማስገባት ሳይችል የቆየው የማዕድን ዘርፍ አሁን ላይ ቢሊዮን ዶላር የሚገኝበት ዘርፍ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ በዚህ ዓመት ከአጠቃላይ ወጪ ንግድ ከ10 ነጥብ 78 እስከ 11 ቢሊዮን ዶላር ገቢ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ የብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፍ ተግባራዊ በመደረጉ ሁሉም ዘርፍ የራሱን ድርሻ እንዲያዋጣ እና ኢኮኖሚው በከፍተኛ ደረጃ እንዲያድግ አድርጓል ነው ያሉት። በመሆኑም በዚህ ዓመት 10 ነጥብ 2 በመቶ የኢኮኖሚ ዕድገት እንጠብቃለን ብለዋል፡፡ ዓመታዊ ገቢ የመሰብሰብ አቅም እጅግ በሚያስደንቅ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት 1 ነጥብ 5 ትሪሊዮን ብር እንደምትሰበስብ ይጠበቃል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፍ አቅጣጫን ተግባራዊ በማድረጓ በሁሉም መስክ ፈጣንና ተከታታይነት ያለው ዕድገት ማስመዝገብ መቻሏን ነው የተናገሩት፡፡ ይህም የመንግስትን ትክክለኛ እና የተሳሰረ የፖሊሲ ተግባራዊ ውጤት ያረጋገጠ ነው ብለዋል፡፡
የቱሪዝም መሰረተ ልማት ግንባታ የሀገሪቱን ስነ ምህዳርና ዘላቂ ልማትን ባገናዘበ መልኩ እየተከናወነ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jun 30, 2026 1272
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 23/2018 (ኢዜአ)፡-የቱሪዝም መሰረተ ልማት ግንባታ የሀገሪቱን ስነ ምህዳርና ዘላቂ ልማት ባገናዘበ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "ቱሪዝም-አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር" በሚል ከኤን ቢ ሲ ኢትዮጵያ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የቱሪዝም መሰረተ ልማት ስነ-ምህዳርን፣ ዘላቂ ቱሪዝምን እና አረንጓዴ ልማትን ባካተተ መልኩ እየተገነባ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የቱሪዝም ዘርፍ ማነቆዎችን ለመፍታት መሰረተ ልማት በአራት ዋና ዋና ክፍሎች ተከፍሎ በትኩረት እየተሰራበት ይገኛል ብለዋል፡፡ በዚህም የመዳረሻ ስፍራዎች ልማት፣ የቱሪስቶች ማረፊያ ቦታዎች፣ የትራንስፖርት መሰረተ ልማት እንዲሁም የዲጂታል መሠረተ ልማቶች መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ባለፉት ጥቂት ወራት ብቻ ሰባት ተጨማሪ ኤርፖርቶች ተመርቀው ስራ የጀመሩ ሲሆን፤ ቀሪዎቹም በቅርቡ ስራ ይጀምራሉ ብለዋል። ባለፉት ስድስትና ሰባት ዓመታት የተከናወኑት የገበታ ፕሮጀክቶች በሀገሪቱ ላይ ትልቅ ተፅዕኖ ማሳረፍ መቻላቸውን ጠቅሰዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በገበታ ለሀገርና ለትውልድ የአርባምንጭ እና የጅማ ፕሮጀክቶች ከሞላ ጎደል ያለቁ ሲሆን፤ የአርባ ምንጭ ፕሮጀክት በቅርቡ ይመረቃል ብለዋል። የኮሪደር ልማትና የሪዞርቶች ተፅዕኖን ሲገልጹም በአርባ ምንጭ፣ በጎርጎራ፣ በሀይቅ፣ በጅማ እና በጅጅጋ (ሸበሌ) የተገነቡት ሪዞርቶችና የኮሪደር ልማቶች የአካባቢውን ከተሞች ገጽታ በመቀየር ረገድ ከፍተኛ ተጨባጭ ተፅዕኖ እያመጡ እንደሚገኙም ጠቅሰዋል፡፡ የቱሪዝም ዘርፉን ለማነቃቃት የተጠቀሟቸው የኢንቨስትመንት ምንጮች እጅግ የተለያዩ ሲሆኑ በሶስት ዋና ዋና ክፍሎች የተከፈሉ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ እነኚህም የመንግስትና የግል አጋርነት፣ የሕዝብ ተሳትፎ እንዲሁም የወዳጅ ሀገራት ድጋፍ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ አሁን ላይ እየታየ ያለው የቱሪዝም ዘርፍ መነቃቃት የዜጎች፣ የግሉ ዘርፍ፣ የውጭ ወዳጅ ሀገራት እና የግለሰቦች የሀብት፣ የሀሳብና የእውቀት ድምር ውጤት መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል።