ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በሲዳማ ክልል በግብርናው ዘርፍ በተከናወኑ ተግባራት እመርታዊ ለውጥ ተመዝግቧል
Sep 6, 2026 223
ሀዋሳ፣ ‎ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በግብርናው ዘርፍ በተከናወኑ ተግባራት እመርታዊ ለውጥ መመዝገቡን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ገለጸ። የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ያለፉት አምስት ዓመታት የዘርፉ አፈጻጸምና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ የሴክተር ጉባኤ ተካሂዷል።   በጉባኤው ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል የመንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ አስፋው ጎኔሶ በክልሉ በግብርናው ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት እመርታዊ ለውጥ ማምጣታቸውን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት ዓመታት የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂና አሰራሮች በመጠቀም የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። በተለይ ህዝብን በማነቃነቅ የማይታረሱ መሬቶች ጭምር እንዲታረሱ ማድረግና አርሶ አደሩን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ በመስኖ በተከናወኑ ተግባራት አመርቂ ውጤቶች መገኘታቸውን ገልጸዋል። በዚህም በመስኖ የሚለማ መሬት መጠን በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩን ገልጸው፣ አርሶ አደሩ በዓመት ከሦስት ጊዜ በላይ በማምረት ከራሱ ባለፈ ለገበያ እያቀረበ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡   የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው እንዳሉት በዘርፉ የ10 ዓመት ፍኖተ ካርታ ተቀርፆ ተግባራዊ እየተደረገ ነው፡፡ በዚህም የምግብና ሥርዓተ ምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ፣ ገበያ ተኮር እና ለኢንዱስትሪዎች ግብዐት የሚሆኑ ምርቶችን በስፋት የማምረትና በእሴት ሰንለት ውስጥ ሰፊ የሥራ ዕድል የመፍጠር ግቦች ተነድፈው በርካታ ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ እነዚህን ግቦች ከማሳካት አንፃርም የተከናወኑ ተግባራት እመርታዊ ለውጥ እያሳዩ መምጣታቸውን አስረድተዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት በቆሎ፣ ገብስ፣ ስንዴና ጤፍን ጨምሮ በሲዳማ ክልል በዋና ዋና ሰብሎች ብቻ የማሳ ሽፋን ከነበረበት 70 ሺህ ሄክታር ወደ 123 ሺህ ሄክታር ማሳደግ እንደተቻለም ተናግረዋል። በቡና ልማትም የተመረጡ ዝርያዎችን በማስፋትና መሰል ሥራዎችን በማከናወን ከአምስት ዓመት በፊት ከነበረበት 149 ሺህ ሄክታር ሽፋን አሁን ላይ 186 ሺህ ሄክታር ማድረስ መቻሉን አስረድተዋል፡፡ በሞዴል አርሶ አደሮች ደረጃ ያለውን የቡና ምርታማነት እድገት ወደ ሁሉም አርሶ አደሮች ለማስፋት በቀጣይ በትኩረት ይሰራል ሲሉም ገልጸዋል። በጉባኤው ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል፡፡      
የግብርና ዘርፍ ምርታማነት የኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ
Sep 6, 2026 271
የግብርና ዘርፍ ምርታማነት የኢትዮጵያ አዲስ ምዕራፍ ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፎች ሁለንተናዊ እና አጠቃላይ የኢኮኖሚ እመርታ በማስመዝገብ ላይ ትገኛለች። በተለይ በግብርና ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ሀገራዊ ምርታማነትን ያሳደገ ውጤት ማስመዝገብ አስችሏል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኢፌዴሪ ሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ እንደተናገሩት፤ በግብርናው ዘርፍ የተከናወኑ ዋና ዋና ስራዎችን የዘርፉን አመርታ ወደ ላቀ ደረጃ አሻግሯል። በግብርናው ዘርፍ ከተከናወኑ ተግባራት መካከል በክላስተር ማረስ፣ የማሽንና የመሬት አጠቃቀምን ማስፋፋት፣ ምርጥ ዘር ማቅረብ እና የሰፋፊ መስኖ ግድቦችን መገንባት ተጠቃሽ ናቸው። ለዚህም ነው የሚታረሰው መሬት መጠን 33 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሄክታር መድረስ የቻለው። በ2017/18 የምርት ዘመን ብቻ 1 ነጥብ 85 ቢሊዮን ኩንታል ምርት መሰብሰብ መቻሉን ከግብርና የተገኘ ማስረጃ ያረጋገጣል። የግብርናውን ዘርፍ ዘመናዊ በማድረግ የዜጎችን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ተስፋ ሰጪ እመርታዎች እየተመዘገቡ ናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ በሀገር ደረጃ ተግባራዊ እየሆነ ያለው የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ አስደናቂ ውጤት እያመጣ ነው። በተለይም በአቮካዶ ምርት ኢትዮጵያ በአፍሪካ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ ከፍተኛ የወጪ ንግድ መሆን ችሏል። ቀደም ሲል በድርቅ እና በረሃብ ይታወቁ የነበሩ አካባቢዎች አሁን የምርት ማዕከል ሆነዋል። በቦረና ከፍተኛ የስንዴ ማሳ የተሸፈነ ሲሆን፤ በሱማሌ እና በአፋር ክልሎች ደግሞ ሰፋፊ እርሻዎች በመስፋፋታቸው በጠንካራ ስራ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል ያሳዩ አከባቢዎች ናቸው። የግብርና ሚኒስትሩ አዲሱ አረጋ በበኩላቸው ስለዘርፉ እድገት ሲናገሩ፤ የሀገሪቷ ግብርና ከሰውና እንስሳት ጉልበት ወደ ሜካናይዜሽን እየተሸጋገረ መሆኑን ገልጸዋል።   ከዚህ ቀደም የነበረውን አነስተኛ የማሽነሪ አጠቃቀም ለመቀየር በወጣው ፖሊሲ መሰረት ከቀረጥ ነፃ ማሽነሪዎችን ማስገባት፣ ለአርሶ አደሮች ብድር ማቅረብ እና የሰው ኃይል ማሰልጠን መቻሉ ለዚህ እንደማሳያ ይጠቀሳል። ባለፉት ዓመታት የመስኖ አውታሮች በመስፋፋታቸው የመስኖ ሽፋን ከዓመት ወደ ዓመት እያደገ መጥቷል። የግብርና ሚኒስትሩ አቶ አዲሱ እንደሚሉት፤ አርሶ አደሩ ዘመናዊ የውሃ ቴክኖሎጂዎችን፣ የውሃ ማከማቸት ዘዴዎችን እና ፓምፖችን በመጠቀም በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ ከማምረት ወደ ሁለት እና ሶስት ጊዜ የማምረት አቅም ላይ መድረሱ ለለውጡ ማሳያ ነው። ይህ እንቅስቃሴ ግብርናው የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም፣ ክረምት ከበጋ ምርት የሚሰጥ እና የምግብ ዋስትናን እንዲሁም የምግብ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ አድርጎታል።   ሽግግርሩ ሰፊ የስራ እድል በመፍጠር፣ የአርሶ አደሩን ገቢ በማሳደግ እና ሀገራዊ የምርት መጠን እንዲጨምር በማድረግ ረገድ እመርታ ማሳየቱን ነው በማስረጃ ተደግፎ የሚገለጸው። ኢትዮጵያ ቀደም ሲል በዝቅተኛ ምርታማነት፣ በረሃብ እና በተረጂነት የምትታወቅ ቢሆንም አሁን ግን በትክክለኛ የፖሊሲ አቅጣጫ እና በመደመር እሳቤ ያንን የቆየ ታሪክ ሽራ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ መጻፍ ጀምራለች ሲሉ ተናግረዋል። ሀገሪቷ በራሷ ጥረት ያመጣችው ይህ የግብርና እመርታ ለአፍሪካ እና ለታዳጊ ሀገራት ትልቅ ምሳሌ መሆን መቻሉን ነው አጽንኦት የሰጡት። አርሶ አደር ሃይሉ ገልገሎ እና ጅሶ ዋጂ ለዚህ ሕያው ምስክር ናቸው። እነርሱ እንደሚሉት በመንግስት ድጋፍ ከበቆሎ ውጪ ስንዴ፣ ቦሎቄ፣ ጤፍ፣ ሽንኩርት እና ሰሊጥ በስፋት ማምረት መጀመራቸው የለውጥ አብነት ነው። ቀደም ሲል በአንድ ሄክታር ያገኙ የነበረው አነስተኛ ምርት አሁን በመንግስት በሚቀርብ ምርጥ ዘር በመጠቀማቸው ከሄክታር እስከ 50 እና 55 ኩንታል ማግኘት ችለዋል። ይህም በትክክል ከፍተኛ ለውጥ እንዳመጣላቸው ይናገራሉ። አርሶ አደር ካሳሁን ዳምጠው እና ሳዲቅ ወለኒኡ አሊ በበኩላቸው፤ በአፋር ክልል የሚገኘው መሬት ማንኛውንም የሰብል ዓይነት መቀበል የሚችል በመሆኑ፣ ያላቸውን መሬት፣ ከብትና የሰው ጉልበት በማስተባበር ማሸላ፣ ሰሊጥ እና ሽንኩርት በስፋት እያመረቱ እንዳለ እማኝነታቸውን ሰጥተዋል። ግብርናው ተቀይሯል። ለውጥም ተመዝግቧል። በግብርና ዘርፍ እየተመዘገበ ያለው እመርታዊ ለውጥ የአዲስ ምዕራፍ መከፈት አብሳሪ ነው።    
በፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ የተመራ ከፍተኛ የመንግሥት ልዑክ ዱባይ ገባ
Sep 6, 2026 272
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፦በኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ የተመራ ከፍተኛ የመንግሥት ልዑክ በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ጉባኤ (AIM Congress) ላይ ለመሳተፍ ዛሬ ማምሻውን ዱባይ ገብቷል። በፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ የተመራው ልዑክ ዱባይ ሲደርስ በአገሪቷ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ደማቅ አቀባበል እንደተደረገላቸው የኢዜአ ሪፖርተር ከሥፍራው ዘግቧል። የኢንቨስትመንት ጉባኤው ከነገ ጳጉሜን 2 እስከ 4 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለሦስት ቀናት በዱባይ ዓለም አቀፍ የንግድ ማዕከል ይካሄዳል። እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2011 የተቋቋመው ይህ የኢንቨስትመንት ጉባዔ ውጤታማ የኢንቨስትመንት የማስተዋወቂያ ስትራቴጂዎችን በማሳደግና ለኢኮኖሚ ምርታማነት እድሎችን በማመቻቸት የዓለምን ኢኮኖሚ ለማጎልበት የሚሰራ የኤም ግሎባል ፋውንዴሽን ኢንሼቲቭ ነው።   በየዓመቱ የሚካሄደው ይህ ዓለም አቀፍ ጉባኤ የኢንቨስትመንት አማራጮችን በማስፋት፣ በአገራት መካከል አጋርነትና የኢኮኖሚ ትብብርን በማጠናከር እንዲሁም በመስኩ የሚስተዋሉ ችግሮችን እልባት በመስጠት በመካከለኛው ምስራቅ ዋነኛ የኢንቨስትመንት መድረክም ሆኖ እያገለገለ ነው። በጉባኤው የአገራት መሪዎች፣ በተለያዩ የዓለም አገራት የሚገኙ ግዙፍ የቢዝነስና ተቋማት ሥራ አስፈጻሚዎች፣ፖሊሲ አውጪዎች፣ ሥራ ፈጣሪዎች፣ የከፍተኛ ትምህርትና የምርምር ተቋማት ተወካዮች፣ሌሎች የዘርፉ ባለሙያዎችና ባለድርሻ አካላት በመድረኩ በጋራ ይመክሩበታል። በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች መንግሥት ከፍተኛ ትኩረት የተሰጠው ዘንድሮ ለ15ኛ ጊዜ በሚካሄደው በዚሁ የዱባይ ጉባኤ ታዳሚዎች በዲጂታል ኢኮኖሚ፣ በዘላቂ ልማትና በስትራቴጂያዊ አጋርነት ላይ ትኩረት አድርገው ይወያያሉ ተብሎ ይጠበቃል። ይህንንም ተከትሎ መድረኩ የዓለምን ኢኮኖሚ ለማጠናከር የሚያስችሉ ውጤታማ ውይይቶችና ግዙፍ የኢንቨስትመንት ስምምነቶች እንደሚያደረጉ ከፍተኛ ግምት ተሰጥቶታል። ኢትዮጵያ በአገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም በተለይም የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን በመሣብና የኢኮኖሚ ትብብሮችን በማጠናከር የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ለማሣደግና ዘላቂ ልማት ለማረጋገጥ እየሠራች ነው።
በባሌ ዞን የግብርና ሜካናይዜሽንን በማስፋፋት የተመዘገቡ እመርታዊ ለውጦች ይጠናከራሉ
Sep 6, 2026 207
አጋርፋ፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፡-በባሌ ዞን የግብርና ሜካናይዜሽንን በማስፋፋት የተመዘገቡ እመርታዊ ለውጦች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገለጸ። በዞኑ የጳጉሜን-1 "የእመርታ ቀን"ን በማስመልከት "እመርታ ለዘላቂ ልማት" በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው የግብርና ልማት ሥራዎች የመስክ ምልከታ በአጋርፋ ወረዳ ተካሂዷል።   በዞኑ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በተሰሩት ሥራዎች እመርታዊ ለውጦች መታየታቸውም ተመልክቷል። በመርሃግብሩ ላይ የባሌ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አልይ መሐመድ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በዞኑ ከተረጂነት ለመውጣትና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ተግባራዊ የተደረጉ ኢንሼቲቮች ውጤት እያስመዘገቡ ነው። በተለይ የኩታገጠም አሰራር፣ ምርጥ ዘር አጠቃቀምና ሌሎች የተሻሻሉ አሰራሮች በስፋት እየተተገበሩ መምጣት የእመርታዊ ለውጡ ማሳያዎች መሆናቸውን አክለዋል።   አቶ አልይ እንዳሉት በዞኑ በ2018/2019 የምርት ዘመን ከ580 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች እየለማ መሆኑን ገልጸዋል። በብልጽግና ፓርቲ የዞኑ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ብርሃኑ አፍራሳ እንዳሉት በዞኑ ባለፉት ዓመታት የግብርና ሜካናይዜሽን በማስፋፋት የተመዘገቡ እመርታዊ ለውጦች ይጠናከራሉ።   በተለይ የኩታገጠም አሰራርን ማስፋት፣ የሰብል ምርትን ማሳደግ፣ የበጋ መስኖን ልማትን ማጠናከርና ዘመናዊ የእንስሳት እርባታን ማስፋፋት አበረታች ውጤት ማምጣቱን ገልጸዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት የግብርና ሜካናይዜሽንና ዘመናዊ የግብርና አሰራርን በማስፋፋት የተመዘገቡ እመርታዊ ለውጦች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አቶ ብርሀኑ አስታውቀዋል። የአጋርፋ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አደም ከድር በሰጡት አስተያየት በ 2 ሄክታር መሬታቸው ላይ በኩታገጠም እያለሙ ካለው የስንዴ ልማት የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።  
የስንዴ አብዮት፦ የኢትዮጵያ ማንሰራራት አብነት
Sep 6, 2026 278
ኢትዮጵያ ዓመታዊ የስንዴ ፍላጎቷ ከ107 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ነው። ይህንን ፍላጎት ለማሟላት ለዓመታት ከ700 ሚሊዮን ዶላር እስከ 1 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ውድ የውጭ ምንዛሬ ለስንዴ ግዢ ስታወጣ ቆይታለች። ከዚህ ቀደም ሀገሪቱ ከዓመታዊ ፍላጎቷ መሸፈን የምትችለው ከ25 እስከ 30 በመቶ የሚሆነውን ብቻ ሲሆን፣ ቀሪውን በውጭ ግዢ ትሸፍን ነበር። በተለይም የዩክሬንና የሩሲያ ጦርነት በዓለም አቀፍ ደረጃ 30 በመቶ የሚሆነውን የስንዴ አቅርቦት በማወኩ ኢትዮጵያ ከባድ የአቅርቦት ፈተና ውስጥ እንድትገባ አድርጓት ነበር። ይህንን የረጅም ጊዜ ተግዳሮት በዘላቂነት ለመቅረፍ መንግሥት የበጋ መስኖ ስንዴ ልማትን በስፋት በመተግበር፣አሲዳማ መሬቶችን በኖራ በማከም እና ረግረጋማ ቦታዎችን በቴክኖሎጂ በማድረቅ ታሪካዊ ለውጥ ለማምጣት እርምጃዎችን ወስዷል። በኩታ ገጠም እርሻና በዘመናዊ ማሽነሪዎች አጠቃቀም የታጀበው ይህ የልማት አብዮት ፍሬ አፍርቶ፣ ኢትዮጵያ ከ2014 ዓ.ም ጀምሮ ከውጭ የምታስገባውን የንግድ ስንዴ ሙሉ በሙሉ አቁማለች። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በስንዴ ልማት የተመዘገበው ስኬት ከውጭ ማስገባትን ማቆም ላይ ብቻ ሳይወሰን፣ ሀገሪቱ ወደ ውጭ መላክ (ኤክስፖርት ማድረግ) የሚያስችል አቅም እንዳላት ያሳየ መሆኑን አመልክተዋል። በዚህም መሠረት የካቲት 5 ቀን 2015 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን በይፋ የስንዴ ኤክስፖርት የተጀመረ ሲሆን፣ ለዚህ ስኬታማነት የተለያዩ ክልሎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርገዋል። ብሔራዊ የማክሮ ኢኮኖሚና የኤክስፖርት ኮሚቴ ሀገሪቱ የሀገር ውስጥ ፍጆታዋን ሸፍና 32 ሚሊዮን ኩንታል ስንዴ ለውጭ ገበያ ማቅረብ የሚያስችል አቅም እንዳላት አረጋግጦ፣የ2.9 ሚሊዮን ኩንታል የውል ስምምነቶች ከረድኤትና ከሀገር ውስጥ ድርጅቶች ጋር ተፈራርሟል። ከሀገር ውስጥ አቅርቦት ባሻገር ኢትዮጵያ በ2015 ዓ.ም ለኬንያ ስንዴ ለመላክ ስምምነት የፈረመች ሲሆን፣ ጅቡቲም ከኢትዮጵያ ስንዴ መግዛት እንደምትፈልግ ገልጻ ከኢትዮጵያ የስንዴ ልማት ብዙ ተሞክሮ እንደምትወስድ አመላክታለች። የአፍሪካ ልማት ባንክ ስንዴ ከውጭ እንደማታስገባ እና ምርቷን ለጎረቤት ሀገራት ማስተላለፍ መጀመሯን በማድነቅ ለአህጉሪቱ እንደ ትልቅ የዕድገት ተሞክሮ አቅርቧል። የአሜሪካ የውጭ ግብርና ቢሮ ሪፖርቶችም በኢትዮጵያ የስንዴ ምርት ዘርፍ ትልቅ እመርታ እያሳየ መምጣቱን ጠቅሰው፣መንግሥት የመስኖ ልማትና የግብርና ኤክስቴንሽን ድጋፍ በማጠናከሩ ሀገሪቱ ከፍተኛ ምርት ማምረቷን አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ዓመታዊ የስንዴ ምርት ከ290 እስከ 340 ሚሊዮን ኩንታል (ከ29 እስከ 34 ሚሊዮን ቶን) በላይ መድረሱ ኢትዮጵያን በአፍሪካ አህጉር ቀዳሚ የስንዴ አምራች ሀገር አድርጓታል። የስንዴ ልማቱ አርሶ አደሩን ከቀድሞው ከእጅ ወደ አፍ ኑሮ አላቆ፣ በኩታ ገጠም እርሻና በሜካናይዜሽን ታግዞ ወደ ሰፋፊ የንግድ ምርት እንዲገባ አስችሏል። የተሻሻሉ የስንዴ የሰብል ዝርያዎች መለቀቃቸው ለዚህ ውጤት ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረከተ ሲሆን፣ የምርት አቅርቦት ሰንሰለቱን ማዘመን በቀጣይነት በትኩረት እየተሠራበት ይገኛል። በምርት አቅም እና በኩታ ገጠም እርሻ የተመዘገቡት እነዚህ ሰፊ ስኬቶች፣ ሀገሪቱ በኢኮኖሚ አቅም እያደረገችው ያለውን ሁለገብ ማንሰራራት በግልጽ የሚያሳዩ አብነቶች ናቸው። ይህ ትልቅ ለውጥ ኢትዮጵያ ከድህነትና ከዕርዳታ ጥገኝነት ወጥታ የምግብ ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ ብቻ ሳይሆን፣ ለሌሎች አፍሪካ ሀገራትም ተስፋ የሚሰጥ አህጉራዊ አርዓያ መሆን መቻሏን አስመስክሯል። ይህ የምርት እመርታ በግብርናው ብቻ ሳይሆን፣ አጠቃላይ የሀገሪቱን ማንሰራራት የሚያረጋግጥ ትልቅ ምዕራፍ ነው። ለዘመናት በውጭ ዕርዳታና በለጋሾች ላይ ተወሰና የነበረችው ኢትዮጵያ፣ዛሬ በራሷ አቅም በመሥራት አህጉራዊ አርዓያ መሆን መቻሏ ትልቅ ስኬት ነው። የኢኮኖሚ ነፃነት እና የሉዓላዊነት ማዕቀፍን በማረጋገጥ ረገድም የስንዴ አብዮቱ የሀገርን አቅም የሚያሳይ ተምሳሌት ሆኗል። በመሆኑም በስንዴ ልማት የተገኘው ይህ ድል የግብርና ዘርፍ ስኬት ብቻ አይደለም፤ ኢትዮጵያውያን በቁርጠኝነትና በትጋት ከሠሩ ሀገርን ማሻገር እንደሚችሉ በተግባር ያረጋገጡበት ታላቅ የሀገር የማንሰራራት ማሳያ ነው።
በአማራ ክልል የግብርናውን ዘርፍ ከአምራች ኢንዱስትሪው ጋር በማስተሳሰር ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ተችሏል
Sep 6, 2026 74
ባህር ዳር፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የግብርናውን ዘርፍ ከአምራች ኢንዱስትሪው ጋር በማስተሳሰር ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። ጳጉሜን 1 - "የእመርታ ቀንን" ምክንያት በማድረግ አምራች ኢንዱስትሪዎችና የሰብል ልማት ተጎብኝቷል። የቢሮው ምክትል ሃላፊ አቶ ቃልኪዳን ሽፈራው በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በክልሉ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ግብርናውን ማዘመንና ግብዓቶችን በወቅቱ ማቅረብ ላይ አተኩሮ እየተሰራ ነው።   በክልሉ የመኸር ወቅት ከ5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያየ ሰብል እየለማ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከዚህም ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ገልፀዋል። የግብርናውን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ለአምራች ኢንዱስትሪዎች ግብዓት በስፋት ማቅረብ እንዲቻል ማስተሳሰር ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ለአብነትም በተያዘው የመኸር ወቅት ለኢንዱስትሪዎች ግብዓት የሚውል አኩሪ አተር በ400 ሺህ ሄክታር፣ በቆሎ በ700 ሺህ ሄክታር እና ስንዴ ደግሞ በ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ እየለማ መሆኑን ጠቅሰዋል። የግብርናን ምርታማነት ለማሳደግ የተፈጠረው ጠንካራ ትስስር በዘርፉ እመርታዊ ለውጥ ለማምጣት ማስቻሉንም ገልጸዋል።   የክልሉ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ተፈሪ ታረቀኝ በበኩላቸው፤ የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት ለማሳደግ በመሰረተ ልማትና የሙያ ድጋፍ ከማድረግ ባሻገር የግብርና ግብዓት በጥራትና በብዛት እንዲያገኙ በትብብር እየተሰራ ነው። በክልሉ የኢንዱስትሪዎች ቁጥር እያደገ ቢመጣም ለውጭ ገበያ የሚቀርቡና ተኪ ምርቶችን እንዲያመርቱ በተደረገላቸው ድጋፍ እመርታዊ ለውጥ ተመዝግቧል ብለዋል። አቶ ተፈሪ እንዳሉት በ2018 በጀት ዓመት 174 ኢንዱስትሪዎች ወደ ማምረት የተሸጋጋሩ ሲሆን ከ3ሺህ 900 በላይ ባለሃብቶችም የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደዋል። የኢንዱስትሪ ዘርፉ እና የግብርና ትስስር በማጠናከሩ ተጨባጭ ውጤት መታየቱን ገልጸው፣ በቀጣይም ይሄ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የ"ኤም ኤስ፣ ኤ ቢዝነስ" ግሩፕ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ አበረ አበራ በበኩላቸው፤ በባህር ዳር የእንስሳት መኖ ማቀነባበሪያ፣ የምግብ ዘይት እና የከረጢት ማምረቻ ፋብሪካዎችን ገንብተው ወደሥራ ገብተዋል። በምርቶቻቸው የገበያ ዋጋ ከማረጋጋት ባለፈ ፋብሪካዎቻቸው የአካባቢ ጥሬ እቃዎችን በግብዓትነት በመጠቀም የገበያ አማራጭ እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቁመዋል። በጉብኝቱ ላይ የተለያዩ ተቋማት ሥራ ሃላፊዎችና ባለሙያዎች የተሳተፉ ሲሆን የአምራች ኢንዱስትሪዎች እንቅስቃሴና በመኸር ወቅቱ የለማ የበቆሎ ሰብል ተጎብኝቷል።    
የኦሮሚያ ክልል ንግድ ቢሮ ለመጪው የዘመን መለወጫ በዓል በፍጆታ ምርቶች ላይ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት ትኩረት ሰጥቷል
Sep 6, 2026 85
አዳማ፤ጳጉሜን1/2018(ኢዜአ)-መጪውን የዘመን መለወጫ በዓል ምክንያት በማድረግ በፍጆታ ምርቶች ላይ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት ለመከላከል ትኩረት መሰጠቱን የኦሮሚያ ክልል ንግድ ቢሮ አስታወቀ። በአዳማ ከተማ ለመጪው የዘመን መለወጫ በዓል የተዘጋጀ ኤግዚቢሽንና ባዛር ተከፍቷል።   የኦሮሚያ ክልል ንግድ ቢሮ ሃላፊ የሺ ጂማ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት፣ በክልሉ የዘመን መለወጫ በዓልን ተከትሎ በፍጆታ ምርቶች ላይ የዋጋ ንረት እንዳይከሰት አምራቹንና ሸማቹን በቀጥታ የሚያገናኝ ኤግዚቢሽንና ባዛር ተከፍቷል። ባዛሩ ለአምራቾች የገበያ ትስስር ከመፍጠር ባለፈ ሸማቾች የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲሸምቱ የሚያስችላቸውና የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የሚያግዝ መሆኑንም ተናግረዋል።   በአዳማ ከተማ ህገ ወጥ ንግድን በመከላከልና ምርቶች ቀጥታ ለሸማቹ እንዲቀርብ በማድረግ በኩል ያለውን ተሞክሮ ወደ ሌሎች የክልሉ ዞኖች ለማስፋፋት እንሰራለን ብለዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ በበኩላቸው እንደገለጹት ከተማ እሰተዳደሩ የሌማት ትሩፋት መርሀግብርን ተግባራዊ በማድረግ አምራቹን ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ ገበያን ለማረጋጋት ትኩረት ሰጥቶ አየሰራ ነው።   በዚህም የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግም በምግብ ራስን ለመቻልና የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉን ጠቁመዋል። የእመርታን ቀን ምክንያት በማድረግ የክልሉ መንግስት አመራሮችና የመስተዳድሩ የሥራ ሃላፊዎች የልማት ሥራዎች ጎብኝተዋል።  
በሶማሌ ክልል የተከናወኑ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት እውን እያደረጉ ነው
Sep 6, 2026 66
ጅግጅጋ፣ጳጉሜን 1/2018(ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተከናወኑ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት እውን እያደረጉ መሆኑን የክልሉ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ሃላፊ አህመድ ረሺድ ገለጹ። በክልሉ ያለውን እምቅ ሃብትና ምቹ እድሎች በመጠቀም በሁሉም ዘርፎች የተቀናጀ የልማት ስራ ተጠናክሮ ቀጥሏል። በዚህም ባለፉት ጥቂት ዓመታት ተጨባጭ ውጤትና ቀጣይነት ያለው ስኬት እየተመዘገበ ህዝቡም ተጠቃሚ መሆን ችሏል። በክልሉ ጳጉሜን 1 "የእምርታ ቀን" እነዚህን ስኬቶች በማስታወስ ለቀጣይ የልማት ስራዎች ይበልጥ ለመትጋት በሚያስችል ሁኔታ እለቱ በጅግጅጋ ከተማ ተከብሯል።   በዚሁ መርሃ ግብር ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት የሶማሌ ክልል የኢንቨስትመንትና የኢንዱስትሪ ቢሮ ሃላፊ አህመድ ረሺድ፤ ከልማት እርቆና ተረስቶ የቆየው የሶማሌ ክልል ያልተቋረጠ ልማት ላይ ይገኛል ብለዋል። በዚህም ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተከናወኑ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት እውን እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። በተጠናቀቀው በጀት አመት ብቻ 530 ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው ወደ ስራ መግባታቸውን ለአብነት አንስተው ከምርትም ባለፈ ለበርካታ ዜጎች ስራ መፍጠሩን ተናግረዋል። የክልሉ የግብርና ቢሮ ምክትል ሃላፊ አብዱረህማን ኑር በበኩላቸው በመደበኛ የምርት ወቅቶችና በመስኖ ጭምር በማልማት የክልሉ የግብርና ምርታማነት እያንሰራራ መምጣቱን ገልጸዋል።   በዚህም የምግብ ዋስትናንና የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የራሱን ድርሻ ማበርከቱን አስረድተዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልሉ የሥራ ሃላፊዎች፣ የንግዱ ማህበረሰብ፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተገኝተዋል።  
የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ የኢትዮጵያን እመርታ በጽኑ መሠረት ላይ እንዲገነባ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ነው
Sep 6, 2026 90
ደሴ፣ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፡-የመደመር መንግሥት የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ የኢትዮጵያን እመርታ በጽኑ መሠረት ላይ እንዲገነባ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑ ተገለጸ። በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት ለማሳደግ ተግባራዊ የተደረጉ የፖሊሲ ማዕቀፎች ተኪ ምርትንና የውጭ ምንዛሬን በማሳደግ ተደማሪ አቅም ፈጥረዋል። በዚህም የገበያ ዋጋን በማረጋጋት አንዲሁም የውጭ ምንዛሬ መዛባትንና የአቅርቦት ችግሮችን በመፍታት በኩል ውጤት አምጥተዋል።   የአምራች ኢንዱስትሪዎች እመርታን በማስመልከት የኮምቦልቻ ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ሥራ አስኪያጅ አቶ አህመድ ሰይድ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ የኢንዱስትሪውን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎች በዘርፉ አመርቂ ውጤት እንዲመዘገብ አድርገዋል። በተለይ የ“ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ ተኪና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በማምረት ረገድ እመርታዊ ለውጥ እንዲመዘገብ ማድረጉን ነው የገለጹት። የመደመር መንግሥት የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ የኢትዮጵያን እምርታ በጽኑ መሠረት ላይ እንዲገነባ የራሱን ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑም አስታውቀዋል እንደ ሥራ አስኪያጁ ገለጻ፣ በልዩ የኢኮኖሚ ዞኑ መሠረተ ልማቶች ተሟልተው ባለሀብቶች እንዲሰማሩ በተደረገው ጥረት በዞኑ ተኪና ለውጭ ገበያ የሚቀረቡ ምርቶች በከፍተኛ ደረጃ እያደጉ መጥተዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ 59 ሚሊዮን ብር የሚገመት የሀገር ውስጥ ተኪ ምርቶችን ማምረት እንደተቻለ አስታውሰው፣ ከወጪ ንግድም 20 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ለሀገር በማስገኘት እመርታዊ ለውጥ ተመዝግቧል ብለዋል ከዚህም ባለፈ በንቅናቄው አማካኝነት የምርት አቅም በማደጉ ከ3 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች አዲስ የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉን አቶ አህመድ ሰይድ አብራርተዋል።   በልዩ ኢኮኖሚ ዞኑ ከተሰማሩ አልሚዎች መካከል የባቲ ትሪዲንግ ኩባንያ ሥራ አስኪያጅ አቶ መስፍን አያሌው በበኩላቸው፤ በ“ኢትዮጵያ ታምርት” ንቅናቄ ታግዘው የጨርቃጨርቅ ክሮችን ማምረት መጀመራቸውን ገልጸዋል። ይህም በገበያው ውስጥ ተወዳዳሪ የምንሆንበትን ትልቅ አቅም ፈጥሮልናል ብለዋል። መንግሥት የኢንዱስትሪውን ዘርፍ ለማሳደግ የቀየሳቸው የአሰራርና የሕግ ማዕቀፎች ምርታማነታቸውን እያሳደገው መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በልዩ ኢኮኖሚ ዞኑ የሚገኘው የትራይባስ ኢትዮጵያ ኩባንያ የሰው ሀብት አስተዳደር ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ሻምበል ደሳለው ናቸው። በዚህም የወንድ ልብሶችን በጥራትና በብዛት በማምረት ወደ አሜሪካ እና ወደ ሌሎች የውጭ ሀገራት በመላክ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እያስገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። ኩባንያው ከውጭ ምንዛሬ ግኝቱ ባለፈ ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ማንሰራራት የድርሻውን እየተወጣ እንደሚገኝም አረጋግጠዋል።  
ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግን ትርፋማ በማድረግ ዘላቂ የሕዝብ ሀብት እንዲሆን የተጀመሩ የሪፎርም ሥራዎች ይጠናከራሉ-አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)
Sep 6, 2026 147
ሎጎ ሐይቅ፤ ጳጉሜን 1/2018(ኢዜአ)፡-ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግን ተወዳዳሪና ትርፋማ በማድረግ ዘላቂ የሕዝብ ሀብት እንዲሆን የተጀመሩ የሪፎርም ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሆልዲንጉ ቦርድ ሰብሳቢ አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለፁ። ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ያለፈው በጀት ዓመት የአፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ትውውቅ መድረክ ዛሬ በደቡብ ወሎ ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ተካሂዷል።   ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩና የሆልዲንጉ የቦርድ ሰብሳቢ አብዱ ሁሴን(ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ሆልዲንጉን በመደገፍና በማጠናከር ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚሸጋገር ዘላቂ የሀብትና ጥሪት ምንጭ ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ ነው። በአደረጃጃት፣ በተሻሻለ አሰራር፣ በጠንካራ ፋይናንስ አሰራር፣ በላቀ ፕሮጀክት አፈጻጸምና በውጤታማ የሪፎርም ትግበራ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በሰባት የኢንቨስትመንት ዘርፎች 46 ኩባንያዎችን አቅፎ የተቋቋመው ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ኩባንያዎቹ ከነበሩበት ችግር በማውጣት ውጤታማ እንዲሆኑ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። መድረኩም የልማት ድርጅቶች ችግሮችን በመፍታት ነገ ጠንካራ የኢኮኖሚ ተቋም በመሆን ለክልሉም ሆነ ለአገራችን እድገት ሚናቸውን እንዲወጡ ለማድረግ ያለመ መሆኑን አስረድተዋል።   የዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ታደሰ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ሆልዲንጉ ድርጅታዊ አቅሙንና የሰው ሃይሉን በማጠናከር ላይ አተኩሮ ስራውን መጀመሩን አውስተዋል። አሰራሩን በዲጂታል ቴክኖሎጂ በማዘመን፣ የአሰራር ግልጽነትና ተጠያቂነትን በማስፈንና አዳዲስ የኢንቨስትመንት እድሎችን በመፍጠር ተስፋ ሰጭ ውጤት እያስመዘገበ ይገኛል ብለዋል። ከተመሰረተ በአንድ ዓመት ቆይታው አደረጃጀት በመፍጠር፣ አሰራር በመዘርጋትና በሌሎች ተግባራት አበረታች ውጤት ማስመዝገቡንም ጠቅሰዋል። የዘመን ኮንስትራክሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ታደሰ ግርማ ድርጅታቸው በኮንስትራክሽን ዘርፉ ተወዳዳሪ በመሆን ለትውልድ የሚተላለፍ ሀብት ለመፍጠር እየተንቀሳቀሰ ይገኛል ብለዋል የጣና ፍሎራ ኩባንያ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ጨርቆስ በበኩላቸው በሰጡት አስተያየት ኩባንያው የተለያዩ የአበባ፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ እያስገኘ መሆኑን ተናግረዋል። ዓባይ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ በስሩ ዘመን ኮንስትራክሽን፣ ዓባይና ፀደይ ባንኮች፣ ጎንደር ብቅል ፋብሪካ፣ ጣና ፍሎራን፣ አምባሰል ንግድ ሥራዎችን ጨምሮ በስሩ 46 ኩባንያዎችን አቅፎ የሚንቀሳቀስ ነው።
በእንስሳት ሀብት ልማት ዘርፍ እመርታዊ ለውጥ ተመዝግቧል
Sep 6, 2026 165
አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፦በእንስሳት ሀብት ልማት ዘርፍ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ ተግባራት እመርታዊ ለውጥ መመዝገቡን የእንስሳት ልማት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አስራት ጤራ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የእንስሳት ተዋፅዖ ምርታማነትን መጨመር ማስቻሉንም ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት በብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፍ ትኩረት ከተሰጣቸው መካከል በግብርናው ዘርፍ የእንስሳት ሃብትና ተዋፅዖ ምርትና ምርታማነት ላይ በተከናወኑ ተግባራት ውጤታ ማስመዝገብ ተችሏል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ይፋ በተደረገው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርም የወተት፣ ዶሮ፣ እንቁላልና ሥጋ፣ በዓሳና በንብ ማርባት ብሎም ማር ምርት ላይ ለውጥ ተመዝግቧል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አስራት (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ከእንስሳት ሀብት የሚፈለገውን ጥቅም ለማግኘት ባለፉት ዓመታት ዘርፈ ብዙ ተግባራት ሲከናወን በመቆየቱ እመርታዊ ለውጥ ተመዝግቧል፡፡ በተለይም በሥጋ ወጪ ንግድ እንዲሁም በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከፍተኛ ስኬት እና ምርታማነት መመዝገቡን ገልጸዋል፡፡ በተለይም የተቀናበሩና ጥራታቸው የተጠበቀ ሥጋና የሥጋ ውጤቶችን ወደ ውጭ በመላክ በኩል ከታቀደው በላይ አፈጻጸም መመዝገቡን ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸው፤ ይህም የዘርፉን አቅም ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋገረ አዎንታዊ እርምጃ መሆኑን ጠቁመዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በወተት፣ በዶሮ እንቁላልና ሥጋ፣ በአሳ እንዲሁም በንብ ማር ምርታማነት ላይ ጉልህ እድገት መመዝገቡን ተናግረዋል፡፡ ይህ ስኬት የሴቶችና የወጣቶችን የሥራ ዕድል ከማስፋት ባለፈ፣ በቤተሰብ ደረጃ የምግብና ስነ-ምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስረድተዋል። በሌማት ትሩፋት፣ በወጪ ንግድ እና በተለይም በእንስሳት ዘርፍ የተመዘገቡት ድሎችና አዎንታዊ ውጤቶች ለቀጣይ ሥራዎች እንደ መስፈንጠሪያ ሆነው እንደሚያገለግሉ ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የተገኙት ስኬቶች የዘርፉን እመርታ ያሳደጉ መሆናቸውን አመልክተው፤ በቀጣይ ሂደት በከፍተኛ ቁርጠኝነትና በላቀ ሞራል ለመስራት ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን አስረድተዋል። ዘንድሮ የተመዘገበውን የምርታማነት መነሻ በማድረግና የተገኙትን ድሎች በማሳደግ የላቀ የምርት ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል፡፡
የእመርታ ቀን ኢትዮጵያ ወደ አምራችነትና ራስን ወደ መቻል የምታደርገው መዋቅራዊ ሽግግር እየተበሰረ ነው
Sep 6, 2026 258
አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 1/2018 ዓ.ም (ኢዜአ)፦ ጳጉሜን 1 የእመርታ ቀን ኢትዮጵያ ከተረጅነትና ከልመና አስተሳሰብ ወደ አምራችነትና ራስን ወደ መቻል የምታደርገውን መዋቅራዊ ሽግግር እያበሰረች መሆኑን የሚያሳይ ነው ሲሉ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) ገለጹ። ዛሬ ጳጉሜን 1 ቀን 2018 ዓ.ም "እመርታ ለኢትዮጵያ ማንሰራራት" በሚል መሪ ቃል "የእመርታ ቀን" በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ይገኛል። በመርሐ ግብሩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የአጋር ድርጅቶች እና የግሉ ዘርፍ ተወካዮች ተገኝተዋል።   የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የእመርታ ቀን አከባበር ኢትዮጵያ ከተረጅነት፣ ከጥገኝነት እና ከልመና አስተሳሰብ ተላቃ ወደ አምራችነትና ራስን ወደ መቻል የምታደርገውን መዋቅራዊና ታሪካዊ ሽግግር የሚያበስር ነው። ሀገሪቷ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ያላትን አቅም በመጠቀም ያከናወነቻቸውን ዓበይት ተግባራትና ያስመዘገበቻቸውን ሁለንተናዊ ስኬቶች ለማሳየት ያለመ መሆኑንም ገልጸዋል። በተለይም የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ስኬቶች፣ የግብርና ምርታማነትን በማረጋገጥ ረገድ የተመዘገቡ ድሎች፣ ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ እና በማዕድኑ ዘርፍ የታዩ ዓበይት እመርታዎች የዚሁ ታሪካዊ ሽግግር አካል መሆናቸውን ጠቁመዋል። ማንሰራራት ማለት ያለፈው ታሪካችን የነበሩትን መልካም እሴቶች ይዞ፣ የነበሩብንን እክሎች በማስተካከልና በዘመናዊ እውቀትና ቴክኖሎጂ በመታገዝ ወደ አዲሱ የከፍታ ምዕራፍ መራመድ ነው ብለዋል። የእመርታ ቀን "እመርታ ለኢትዮጵያ ማንሰራራት" በሚል ስናከብር ለኢትዮጵያ ብልፅግና እና ለአዲሱ መንግሥት የልማት አጀንዳዎች ትልቅ ግብዓት እንደሚሆኑ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶቻችንን ለማስተዋወቅና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ምቹ አጋጣሚ ፈጥሮልናል - የኤክስፖ ተሳታፊዎች
Sep 6, 2026 136
አሶሳ፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶቻችንን ለማስተዋወቅና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ምቹ አጋጣሚ ፈጥሮልናል ሲሉ በአሶሳ ከተማ በተካሄደው ኤክስፖ ምርቶቻቸውን ያቀረቡ ተሳታፊዎች ገለጹ። ከነሃሴ 27/2018 እስከ ጳጉሜን 1/2018 "ከመሸመት ወደ ማምረት" በሚል መሪ ሃሳብ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ አሶሳ ከተማ ሲካሄድ የቆየው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ተጠናቋል።   የኤክስፖው ተሳታፊዎች የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶቻችንን በማስተዋወቅ ባሻገር ቀጣይነት ያለው የገበያ ትስስር ለመፍጠር የሚያስችል እድል አመቻችቶልናል ብለዋል። ከተሳታፊዎቹ መካከል አፈወርቅ ዴሬሳ፤ ኤክስፖው ምርቶቻቸው የበለጠ እንዲተዋወቁ ከማድረግ ባለፈ በራስ አቅም የሚመረቱ የውበት መጠበቂያ ውጤቶች ትኩረት እንዲያገኙ አድርጓል ሲሉ ተናግረዋል። የድርጅታቸው ምርት በአፍሪካ ደረጃ ተወዳዳሪ በመሆን ዕውቅና ማግኘቱን ገልጸው በአካባቢው የሚገኙ የተፈጥሮ ሀብቶችን በመጠቀም ሳሙና፣ ሽቶ እና የተለያዩ አይነቶች የውበት መጠበቂያ ውጤቶችን እያመረቱ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሌላው የግብርና ውጤቶችን በማቀነባበር በኤክስፖው የተሳተፈው የአሶሳ ግብርና ቴክኒክ ሙያ ማሰልጠኛ ኮሌጅ ሲሆን ኮሌጁ የማር ምርት እና ሌሎች የግብርና የተቀነባበሩ የግብርና ውጤቶችን በማቅረብ ተሳትፈዋል። በኮሌጁ የእንስሳት እርባታ የትምህርት ክፍል ሀላፊ ዙምራ ሰኢድ፤ ኮሌጁ በተግባር የታገዘ የመማር ማስተማር ስራን ተግባራዊ በማድረግ እሴት የተጨመረባቸውን የግብርና ምርቶች ወደ ገበያ ለማቅረብ እየሰራ ነው ብለዋል። የዲአርቢ እምነበረድ ፋብሪካ ፋብሪካ የምርት ክፍል ድንበሩ መኮንን በበኩላቸው፤ ፋብሪካው እምነበረድን በተለያዩ ቅርጾች በማዘጋጀት ለገበያ እያቀረበ መሆኑን ገልጸው ኤክስፖው የፋብሪካውን የስራ እንቅስቃሴ ማስተዋወቅ ያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል።   የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ አመንቲ ገሺ፤ ኤክስፖው በክልሉ እያንሰራራ የሚገኘውን የኢንዱስትሪ ዘርፍ የበለጠ ውጤታማ የሚያደርግ እና ባለሃብቶችን በተለያዩ የልማት ዘርፎች ለመሳብ ያግዛል ብለዋል። ኤክስፖው በክልሉ የሚገኙ የተፈጥሮ ሀብቶች ወደ ልማት እየተቀየሩ መሆናቸውን በተግባር ያሳዬ እና በቀጣይ የኢንዱስትሪ ዘርፉን የበለጠ ለመደገፍ የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይም የኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ዘርፉ የሚጠይቀው መሠረተ ልማት በማሟላት ለዘርፉ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል።      
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ዘመናዊ ግብርናን በማስፋፋት የተመዘገቡ እመርታዊ ለውጦች ይጠናከራሉ
Sep 6, 2026 265
ሆሳዕና፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ዘመናዊ ግብርናን በማስፋፋት የተመዘገቡ እመርታዊ ለውጦች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የጳጉሜን 1 "የእመርታ ቀን"ን በማስመልከት "እመርታ ለዘላቂ ልማት" በሚል መሪ ቃል ያዘጋጀው የግብርና ልማት ሥራዎች የመስክ ምልከታ በከምባታ ዞን ተካሂዷል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የማኅበረሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ናቸው፡፡ በክልሉ ባለፉት ሦስት ዓመታት ዘመናዊ ግብርናን ለማስፋፋት በተሠሩ ሥራዎች ተጨባጭ እመርታዊ ለውጦችን ለማስመዝገብ መቻሉንም ጠቁመዋል። በክልሉ የማሳ ሽፋን በ2016 በጀት ዓመት 980 ሺህ ሄክታር መሬት እንደነበር አቶ ኡስማን አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ ለማድረስ ተችሏል ብለዋል። ዓመታዊ የምርታማነት መጠን 106 ሚሊዮን ኩንታል ከነበረበት ወደ 161 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ማሳደግ እንደተቻለም ተናግረዋል። እንደ አቶ ኡስማን ገለጻ የሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር ትግበራው የእንስሳት፣ የማር፣ የዶሮና የእንቁላል ምርታማነት እንዲጨምር ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል። የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል የወተት ምርታማነትን ማሳደግ በመቻሉ የአርሶ አደር የወተት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪዎች አገልግሎት መስጠት እንደጀመሩም ተናግረዋል። የዘመኑ አርበኝነት ከድህነት መውጫ መንገዶችን አሟጦ በመጠቀም ውጤታማ መሆን እንደሆነ ያነሱት ኃላፊው፣ በዘርፉ እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል የሁሉም ርብርብ ያስፈልጋል ብለዋል። የከምባታ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ተሾመ ሄራም በበኩላቸው እንዳሉት፣ በዞኑ ባለፉት ዓመታት በግብርና መስክ ያሉ ዕድሎችን አሟጦ ለመጠቀም በተሠሩ ሥራዎች ውጤት ተመዝግቧል። በተለይም የሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር መተግበሩ በዞኑ ከ850 በላይ የወተት፣የዶሮ፣ የንብና የማር መንደሮች መደራጀታቸውን ጠቁመዋል። የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚያግዙ ሰብሎችን በስፋት ከማልማት በተጨማሪ የሀገርን ኢኮኖሚ የሚደግፉ ቡናና የቅመማ ቅመም ምርቶች እንዲመረቱ አስቻይ ሁኔታዎች መፈጠራቸውንም አስረድተዋል። በዘርፉ እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶችን አጠናክሮ በማስቀጠል ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን የማረጋገጥ ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል። በዱራሜ ከተማ በጥምር ግብርና የተሰማሩት ወይዘሮ ተዋበች ታደሰ አራት ሄክታር ማሳቸውን በጥምር ግብርና በማልማት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይም ለኤክስፖርት የሚሆን ቡና እና ማር እያመረቱ እንደሚገኙ ገልጸው፣ በዘርፉ እየተደረገላቸው ባለው ድጋፍ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልል፣ የከምባታ ዞንና የዱራሜ ከተማ ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል።
በደብረ ብርሃን ከተማ 29 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ተሰማርተዋል
Sep 6, 2026 75
ደብረ ብርሃን ፤ጳጉሜን 1/2018(ኢዜአ)፡- በደብረ ብርሃን ከተማ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 29 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች መሰማራታቸውን የከተማ አስተዳደሩ አንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ገለጸ። የኢንዱስትሪ ዘርፉን ምርታማነት በማሳደግ ለዜጎች ተጠቃሚነትና የሀገር እድገት መሰረት እንዲሆን ባለፉት ጥቂት አመታት ከፖሊሲ ለውጥ ጀምሮ የተለያዩ ተግባራት ተከናውነዋል። በዚህም ዘርፉ እመርታ እያስመዘገበ የበርካታ ዜጎች የስራ መስክና የውጭ ምንዛሬ ወጪን በመቀነስም የላቀ አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል። በአማራ ክልል የደብረ በርሃን ከተማ የኢንዱስትሪ ማእከል ሆና በርካታ ኢንቨስተሮችን እያስተናገደች እድገትና ማንሰራራት እያሳየች ትገኛለች። ከዚሁ ጋር በተገናኘ ኢዜአ ያነጋገራቸው የደብረብርሃን ከተማ አስተዳደር የኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ሃላፊ ብርሃን ገብረህይወት፣ በከተማዋ የኢንቨስትመንት ዘርፉ በርካታ ባለሃብቶችን በመሳብ ለውጥና እድገት በማሳየት ላይ መሆኑን ገልጸዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ 29 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ መሰማራታቸውን ጠቅሰዋል። በአምራች ኢንዱስትሪ፣ በአገልግሎት፣ በግብርና በማዕድን እና በሌሎችም ዘርፎች የኢንቨስትመንት ፈቃድ በመውስድ ወደ ስራ መግባታቸውን አንስተው እስካሁን 22 ኢንዱስትሪዎች ወደ ምርት መግባታቸውን ገልጸዋል።   በጨርቃጨርቅ፣ በቆዳና ሌሎችን ጨምሮ በዓመቱ ለውጪ ገበያ ከቀረበው ምርታቸው 137 ሚሊየን ዶላር ገቢ መገኘቱን ጠቅሰዋል። ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ የሚተካ 70 ሺህ 636 ቶን ተኪ ምርት በማምረት ለሀገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ የታቸለበትን ስኬትም አንስተዋል። በዚህም 589 ሚሊየን ዶላር የውጪ ምንዛሬ ማዳን መቻሉን የገለጹት ሃላፊው የዘርፉን እመርታ የሚያሳዩ በርካታ ውጤታማ መገለጫዎች መኖራቸውን ተናግረዋል።   በኢንዱስትሪ ዘርፍ ከተሰመሩ ባለሃብቶች መካከል በላይነህ ቢዝነስ ግሩብ የፊቤላ ደብረብርሃን መኪና መገጣጠሚያ ስራ አስኪያጂ አቶ መሐመድ አህመድ፤ በዘርፉ የተፈጠረው ምቹ ሁኔታና የመንግስት ድጋፍ ታክሎበት ዘርፉ ውጤታማ መሆኑን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ዘርፉ ለበርካታ ሰዎች የስራ እድል እየተፈጠረበት፣ የእውቀት ሽግግርና የውጭ ምንዛሬ እየተገኘበት እንዲሁም የሀገር ውስጥ የምርት ፍላጎት እየተስተናገደበት ይገኛል ብለዋል።  
ኢትዮጵያ እመርታዊ ውጤቶችን እያስመዘገበች ወደ ላቀ ብልፅግና እየተጓዘች ትገኛለች-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Sep 6, 2026 246
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 1/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ እያመረተች በርካታ እመርታዊ ውጤቶችን እያስመዘገበች ወደ ላቀ ብልፅግና እየተጓዘች ትገኛለች ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፎች የጀመረችውን ሁለንተናዊ የለውጥና የብልፅግና ጉዞ በማጠናከር ከተረጅነት ወደ አምራችነት በጽኑ መሸጋገር ላይ እንደምትገኝም ተናግረዋል። ዛሬ ጳጉሜን 1 ቀን 2018 ዓ.ም "እመርታ ለኢትዮጵያ ማንሰራራት" በሚል መሪ ቃል "የእመርታ ቀን" በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ይገኛል።   በመርሐ ግብሩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የአጋር ድርጅቶች እና የግሉ ዘርፍ ተወካዮች ተገኝተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በዚሁ ወቅት፤ ባለፉት ዓመታት የተተገበሩት የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎችና የፋይናንስ ሥርዓት ማዘመኛ እርምጃዎች የኢኮኖሚውን መሠረት ማጠናከራቸውን ገልጸዋል። በተለይም የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት እመርታዊ ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል። በዚህም በሥጋ፣ በሩዝ፣ በበቆሎ፣ በወተት እና በሌሎችም ሰብሎች በሌማት ትሩፋትና በክላስተር እርሻ አማካኝነት የተመዘገቡት ስኬቶች የኢትዮጵያን ምግብ የማምረት አቅም ማሳደጋቸውን ገልጸዋል። በማኑፋክቸሪንግና አግሮ ኢንዱስትሪ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄና በኢንዱስትሪ ፓርኮች አማካኝነት የውጭ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት በመተካት ኢትዮጵያን ከሸማችነት ወደ አምራችነትና ተወዳዳሪነት መዋቅራዊ ሽግግር ማድረጓን ተናግረዋል። በማዕድን ዘርፍ የተፈጥሮ ሀብትን በእሴት ጭማሪ ወደ ከፍተኛ ኢኮኖሚ በመለወጥ አዳዲስ የኤክስፖርት ዕድሎች መፈጠራቸውን አብራርተዋል። በገቢዎችና ጉምሩክ ዘርፍ የኢ-ፋይሊንግ፣ የኢ-ፔይመንት እና የአሠራር ዲጂታላይዜሽን ግልጽነትና ቅልጥፍናን በማምጣት የታክስ ሕግ ተገዥነትን ማጠናከራቸውን ጠቁመዋል። አምራችነት እሳቤ፣ ስልት እና ግብ መሆን እንዳለበት ያሰመሩበት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ማናቸውም ሥራ እና ፕሮጀክት እሴት ካልጨመረና ምርት ካላተረፈረፈ ብክነት እንደሆነ ገልጸዋል።   የአገልግሎት አሰጣጥን ከእጅ መንሻና ከሙስና ነጻ ለማድረግ አሠራሮችን ወደ ዲጂታል ማሸጋገር እንደሚገባም አሳስበዋል። ኢትዮጵያ እየተለወጠች፣ እያንሰራራች፣ እያመረተች ወደ ላቀ ብልጽግና እየተጓዘች እንዳለች ተናግረው፤ ለዚህ የኢትዮጵያ ከፍታ በተሰማሩበት ዘርፍ ሌሊትና ቀን ለደከሙ ኢትዮጵያውያን፣ የኢትዮጵያ ወዳጆች እና አጋሮች ሁሉ ምስጋና አቅርበዋል።
የአፋር ክልልን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት በማልማት የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ ነው
Sep 6, 2026 63
ሰመራ፣ጳጉሜን 1/2018(ኢዜአ) ፡-የአፋር ክልልን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት በማልማት የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የመሬት ቢሮ ኀላፊ ኡመር ኑር ገለጹ። "የእመርታ ቀን" በአፋር ክልል ሰመራ ከተማ በተለያዩ መርሃ ግብሮች እየተከበረ ይገኛል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የአፋር ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የመሬት ቢሮ ኀላፊ ኡመር ኑር ፤ የአፋር ክልል ብዙም ሳይለማ የቆየ ሰፊ መሬትና እምቅ የተፈጥሮ ሃብት ያለው መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ በተለይም በመስኖ ሊለማ የሚችል ሰፊ መሬት መኖሩን በማንሳት ባለፉት ጥቂት ዓመታት የበጋ መስኖን ጨምሮ ሌሎችም የግብርና ልማት ስራዎች መከናወናቸውን አንስተዋል። የመሰኖ ስራዎችን በማጠናከር መሬት በተጠናከረ አቅም ወደ ምርት ለማስገባት በሚደረገው ጥረት በርካታ ወጣቶች እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸው ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት የመውጣት ጥረት በተሳካ ሁኔታ መቀጠሉን ተናግረዋል። የአርብቶ አደሩን ማህበረሰብ አኗኗር መሰረት ያደረጉ የልማት ስራዎች በመጠናከር ተጠቃሚ ማድረግ በመቻሉ ከተረጅነት የመውጣት ጥረት ጥሩ መሰረት እየያዘ መሆኑን ገልጸዋል። የአፋር ክልልን ሰፊ መሬትና እምቅ የተፈጥሮ ሃብት በማልማት የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን ተናግረዋል።   የአፋር ክልል የፕላንና ልማት ቢሮ ምክትል ኀላፊ አብዱ መሐመድ፤ ባለፉት ስምንት ዓመታት አፋር ክልልን የተለየ ገፅታ ያላበሱ ስኬታማ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል ብለዋል። በተለይም በግብርና ፣ኢንዱስትሪ በማዕድንና አንሰሳት ልማት እመርታዊ ስኬት ስለመመዝገቡ ተናግረዋል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት በየደረጃው ያሉ የክልሉ አመራሮችና የሠመራ ሎጊያ ከተማ ነዋሪዎች የችግኝ ተከላ አካሂደዋል።
በአማራ ክልል የሚከበሩ ህዝባዊና ኃይማኖታዊ በዓላት የቱሪስት ፍሰቱን ጨምረዋል
Sep 6, 2026 64
ባህር ዳር፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ) ፦ በአማራ ክልል በአደባባይ የሚከበሩ ህዝባዊና ሀይማኖታዊ በዓላት የቱሪስት ፍሰትን በመጨመር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያሳደጉ መምጣታቸውን የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋንቱ ተስፋዬ ገለጹ። የሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል፣ ቡሄና እንግጫ ነቀላ በዓላት የመዝጊያ መረሃ-ግብር "ባህላዊ እሴቶቻችን የፈተና መሻገሪያ የጋራ ተስፋችን መገንቢያ" በሚል መሪ ሀሳብ ዛሬ ተከናውኗል።   የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋንቱ ተስፋዬ በመርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት የአማራ ክልል የበርካታ የተፈጥሮ፣ የሰው ሰራሽ፣ ባህላዊና ሃይማኖታዊ እሴቶች ባለቤት ነው። ከዚህ መካከል ሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል፣ እንግጫ ነቀላ፣ ቡሄና ሌሎች በአደባባይ የሚከበሩ በዓላት የቱሪስት ፍሰቱን ዓመቱን ሙሉ በማድረግ ዘላቂ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዓላቱን ለቱሪስት መስህብነት በማዋል የኢኮኖሚ ጠቀሜታቸውን ከማሳደግ ባለፈ የሕብረ ብሔራዊነት መገለጫነታቸውን ለማጉላት ይበልጥ መስራት እንደሚገባ አስረድተዋል።   በቀጣይም የበዓላቱን እሴት ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ ባለድርሻ አካላት ሀላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው የሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለልና እንግጫ ነቀላ በዓላት የልጃገረዶች አንድነትና ነጻነት ደምቆ የሚታይበት ነው። በዓላቱ የፍቅር፣ የመተሳሰብና የትብብር እሴቶች መገለጫ በመሆናቸው፣ ጠብቆ ለትውልድ ለማስተላለፍ እየተሰራ ያለው ስራ የሚበረታታ መሆኑን አስረድተዋል።   የአማራ ክልል ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ መልካሙ ፀጋዬ በበኩላቸው በዓላቱ የተስፋ፣ የነጻነትና የትብብር ተምሳሌት መሆናቸውን አስታውሰው፣ የክልሉን እምቅ የቱሪዝም ሀብት አጉልቶ ለማሳየት ያስችላሉ ብለዋል። ባህላዊ እሴቶቹን ለማህበረሰባዊ ትስስር ለማዋል ከባለ ድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም አስረድተዋል። በድምቀት በተከበረው የቡሄ፣ ሻደይ፣ አሸንድዬ፣ ሶለል እና እንግጫ ነቀላ የመዝጊያ ሥነ ስርአት ላይ የክልሉ አመራሮችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያ እየተከተለችው ያለው ብዝሃ መር የኢኮኖሚ ልማት ስትራቴጂ ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው
Sep 6, 2026 84
ዲላ፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ) ፦ኢትዮጵያ እየተከተለችው ያለው ብዝሃ መር የኢኮኖሚ ልማት ስትራቴጂ ተጨባጭ ውጤት እያመጣ መሆኑን ኢዜአ ያነጋገራቸው የዘርፉ ምሁራን ገለጹ። ቀደም ሲል በግብርና መር ኢኮኖሚ ልማት ላይ ተወስና የቆየችው ኢትዮጵያ በመደመር መንግሥት ወደ ብዝሃመር የኢኮኖሚ ልማት ስትራቴጂ ተሸጋግራለች። የኢትዮጵያን እምቅ የመልማት አቅሞች በመገንዘብ የግብርና ልማትን ጨምሮ በኢንዱስትሪ፣ ቱሪዝም፣ አይሲቲና የማዕድን ዘርፍ ዋነኛ የልማት ምሰሶዎች ሆነው እየተሰራባቸው ይገኛሉ። በእነዚህ ዘርፎችም ላይ በተሰሩ ስራዎች ሀገሪቱ እመርታዊ እድገትና ማንሰራራት ላይ ለመሆኗ በርካታ ተጨባጭ ማሳያዎችን መጥቀስ ይቻላል። በዲላ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንትና የተፈጥሮ ሃብት ተመራማሪ ሐብታሙ ተመስገን (ዶ/ር)፤ የልማት ስትራቴጂው ብዝሃ መሆኑ እና ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም መደረጉ ለተመዘገበው ስኬት የላቀ ትርጉም አለው ብለዋል። የብዝሃ ኢኮኖሚ እድገት አማራጭን ከመከተል ባለፈ በተለይም በግብርናው ዘርፍ አዳዲስ ኢንሼቲቮችን በመተግበርና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ ትልቅ እመርታ መታየቱን አስረድተዋል። በስንዴ ልማት፣ በቡና ልማት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም ሌሎች የግብርና ዘርፎች ውጤቱና ስኬቱ አስደናቂ መሆኑን ነው ያነሱት። የተፈጥሮ ሃብትና መሬት አስተዳደር ተመራማሪና የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት ፤ እምቅ የተፈጥሮ ሃብቶችን በመጠቀም እየተሄደበት ያለው የልማት ዕቅድ በአጭር ጊዜ ውጤት አምጥቷል። በተለይም በግብርናው ዘርፍ የተጀመረው የተቀናጀ የልማት ጥረት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነትና በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ መሰረት መሆኑን አንስተዋል። ከመደበኛ የምርት ወቅት በተጨማሪ የመስኖ ልማት ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸው፣ የዘርፉ እመርታ በተጠናከረ መልኩ እንደሚቀጥልም ያላቸውን እምነት ተናግረዋል። በኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ የታየው እመርታ ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጂነት ለመውጣትና ጠንካራ ኢኮኖሚ ለመገንባት መሰረት የሚጥል መሆኑን ምሁራኑ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ በችግር ውስጥ ዕድልን፣ በጉድለት ውስጥ አቅምን ፈልጋ የማግኘት ታሪካዊ ጽናት አላት- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Sep 6, 2026 144
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በችግር ውስጥ ዕድልን፣ በጉድለት ውስጥ አቅምን፣ በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ተስፋን ፈልጋ የማግኘት ታሪካዊ ጽናት አላት ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። የኢትዮጵያ ማንሠራራት፡ ከዕድል ወደ እመርታ፣ ከእመርታ ወደ ከፍታ በሚል መለዕክት ያስተላለፉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ዛሬ የኢትዮጵያን ማንሠራራት የሚያመላክተውን የጳጉሜን 1 የእመርታ ቀን አክብረናል ብለዋል። ኢትዮጵያ ከቆመችበት ከተነሣች እና ከተንቀሳቀሰች ቆይታለች፤ አሁን በሙሉ አቅሟ ወደ ላቀ ከፍታ እያንሠራራች ያለችበት ጊዜ ላይ እንገኛለን ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ኢትዮጵያ በችግር ውስጥ ዕድልን፣ በጉድለት ውስጥ አቅምን፣ በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ተስፋን ፈልጋ የማግኘት ታሪካዊ ጽናት አላት ብለዋል። የዛሬው እመርታችን የትናንት ቁርጠኝነታችን ፍሬ ነው፤ የነገው ከፍታችን ደግሞ የዛሬ ትጋታችን ውጤት ይሆናል። በግብርና የምግብ ሉዓላዊነታችንን እያረጋገጥን፣ በኢንዱስትሪ ከሸማችነት ወደ አምራችነት እየተሸጋገረን፣ በማዕድን ዘርፍ የተፈጥሮ ፀጋችንን በዕሴት ጭማሪ ወደ ሀገራዊ ሀብት እየቀየርን እንገኛለን። በዲጂታል ለውጥና የአገልግሎት አሠራር ዘመናዊነትም ጠንካራ የኢኮኖሚ መሠረት ጥለናል። ይህ ጉዞ ከጥገኝነት ወደ ራስን መቻል የሚያሸጋግር የኢትዮጵያ የእመርታ ጉዞ ነው። ለእኛ አምራችነት ዕሳቤም፣ ስልትም፣ ግብም ነው። ሥራችን፣ ንግግራችን እና ፕሮጀክቶቻችን ሁሉ ዕሴት የሚጨምሩና ምርት የሚያስገኙ መሆን አለባቸው። ዛሬ ያገኘነውን እመርታ ወደ ነገ ከፍታ ለመቀየር የበለጠ መሥራት፣ የበለጠ ማምረት፣ የበለጠ መፍጠር እና መፍጠን ይጠበቅብናል። በወጣቶቻችን እውቀት፣ በአምራቾቻችን ቁርጠኝነት እና በሕዝባችን አቅም ራሷን የቻለችና የማትበገር ኢትዮጵያን እንገነባለን። የኢትዮጵያ ማንሠራራት ይቀጥላል፤ እመርታው ይፋጠናል።የኢትዮጵያ ከፍታ አይቀርም ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም