ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በክልሉ የአርሶ አደሩን ምርታማነት በማሳደግ ወደ ኢንቨስትመንት ለማሸጋገር የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስመዘገቡ ነው
Jul 26, 2026 99
ደብረ ብርሃን፤ሐምሌ 19/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የአርሶ አደሩን ምርታማነት በማሳደግ ወደ ኢንቨስትመንት ለማሸጋገር የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያስመዘገቡ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ(ዶ/ር) ገለጹ። በሰሜን ሸዋ ዞን በሞረትና ጅሩ ወረዳ የሚገኙ 837 አርሶ አደሮችን ያቀፈው ማህበር “የጅሩ-አግሮ ቢዝነስ“ ኩባንያን ዛሬ መሰረተ። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ(ዶ/ር) በምስረታው ወቅት እንደገለጹት፤ ኩባንያው የአርሶ አደሮችን ምርት በማቀነባበርና እሴት በመጨመር ለገበያ የሚያቀርብ ነው። አርሶ አደሮቹ በማህበር ተደራጅተው የራሳቸውን አግሮ - ቢዝነስ ኩባንያ ማቋቋማቸው ከግብርና ወደ ኢንዱስትሪ የሚደረገውን የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር ለማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ይህም አርሶ አደሮቹን ከጥሬ ግብአት አቅራቢነት ወደ አምራች ኢንዱስትሪ ኢንቨስተርነት በማሳደግ ተጠቃሚነታቸውን ይበልጥ የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ በበኩላቸው፤ የግብርናውን ምርታማነት በማሳደግ ለኢንዱስትሪ ግብአትና ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት የተሰራው ስራ ውጤታማ ሆኗል ብለዋል። የተመሰረተው የቢዝነስ ኩባንያም ውጤታማ የሆኑ አርሶ አደሮችን ምርት በጥሬው ከማቅረብ ይልቅ እሴት ጨምሮ ለገበያ በማቅረብ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የሚያስችል ነው ብለዋል። ኩባንያው የዱቄት ፋብሪካ በማቋቋምና ዱቄት በማምረት በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ፣ ትራክተርና ሌሎች ቴክኖሎጂዎችን ለማስመጣትና በሌሎች የስራ ዘርፎች በመሰማራት ዘርፉን ለማዘመን ያስችላል ብለዋል። በምስረታው ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ምክትል ጀኔራል ዳይሬክተር ፍሬው ተገኘ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አርሶ አደሮቹ ትራክተርና ሌሎች የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመው ዘርፉን በማዘመን ውጤታማ እየሆኑ ነው ብለዋል። ኩባንያው መመስረቱም የኢንቨስትመንት ብድር በቀላሉ በማግኘት ፈጥነው የግብርና ምርቶችን በማቀነባበር በከፍተኛ ዋጋ ለሀገር ውስጥና ለውጪ ገበያ ለማቅረብ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። እንደ ሀገር 50 የአግሮ ኢንዱስትሪ ኩባንያ ለመገንባት መታቀዱን ጠቁመው በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን በዛሬው እለት የተመሰረተው ይህ ኩባንያ አንዱ መሆኑን አመልክተዋል። የሰሜን ሸዋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ተክለየስ በለጠ እንደገለጹት፤ የኩባንያው መመስረት የአርሶ አደሩንና የቤተሰቦቻቸውን ኑሮ ከማሻሻሉም በላይ ፈጣን እድገት እንዲመዘገብ አስተዋጽኦ ያበረክታል። የዞኑ አስተዳደርም የተመሰረተው ኩባንያ ውጤታማ ሆኖ ለሌሎች አካባቢዎች ሞዴል እንዲሆን አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
በክልሉ የዜጎችን ጥያቄ የሚመልሱ የልማት ስራዎችን በመተግበር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ይሰራል
Jul 26, 2026 72
ቦንጋ ፤ሐምሌ 19/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የዜጎችን ጥያቄ የሚመልሱ የልማት ስራዎችን በመተግበር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለፁ። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በኮንታ ዞን አመያ ዙሪያ ወረዳ በ85 ሚሊዮን ብር የተገነባው የኡማ ድልድይ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደገለፁት፣ የዜጎችን ጥያቄዎች የሚመልሱ ትልልቅ የልማት ስራዎችን በማቀድና ወደ ተግባር በመቀየር የማህበረሰቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው። የክልሉ መንግስት ለፕሮጀክቱ ትኩረት በመስጠትና የነበሩ ችግሮችን በመፍታት በአጭር ጊዜ ውስጥ አጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ ማስቻሉን ተናግረዋል። ድልድዩ አርሶአደሩ በፍራፍሬ እና በእንስሳት ልማት እንዲሁም በእርሻ ስራ ላይ በሰፊው በመሰማራት የኢኮኖሚና ማህበራዊ እንቅስቃሴው ምቹ እንዲሆን ያስችላል ብለዋል፡፡ በሚከናወኑ የልማት ስራዎች የሕብረተሰቡ ተሳትፎ እያደገ የመጣ በመሆኑ ይህን አጠናክሮ በማስቀጠል የማህበረሰቡን ጥያቄዎች ለመመለስ የሚያስችሉ ተግባራትም ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ፋጂዮ ሳፒ በበኩላቸው፤ ክልሉ ከተመሰረተ ወዲህ 20 የተለያየ ደረጃ ያላቸው ድልድዮች ተገንብተው ወደ ስራ መግባታቸውን አስታውሰዋል፡፡ ዛሬ የተመረቀው የኡማ ድልድይ ግን በርዝማኔው የመጀመሪያ መሆኑን ገልፀዋል። ከሁለት ዓመት በፊት ግንባታው የተጀመረው የ84 ሜትር ርዝመት ያለው የኡማ ወንዝ ድልድይ ከ85 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበትም ተናግረዋል። የኡማ ወንዝ ሞልቶ በርካታ የልማት ስራዎችንና ማህበራዊ እንቅስቃሴዎችን ሲያስተጓጎል መቆየቱን የገለፁት ደግሞ የኮንታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታከለ ተስፉ ናቸው። አካባቢው ሰፊ የመልማት አቅም ያለው ነው ያሉት አቶ ታከለ፣ ድልድዩ ይህን ወደ ኢኮኖሚ በመቀየር፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችን የሚያሳልጥ መሆኑን ተናግረዋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ፍቅሬ አማንን ጨምሮ የክልል፣ የዞንና የወረዳው ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክርቤት ለ2019 በጀት ዓመት ከ25 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት አጸደቀ
Jul 26, 2026 135
አሶሳ፤ ሐምሌ 19/2018 (ኢዜአ)፡- የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክርቤት በመጨረሻ ቀን የጉባዔ ውሎው ለ2019 በጀት ዓመት ከ25 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት አጽድቋል። ለሁለት ቀናት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ሲመክር የቆየው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክርቤት በዛሬው የመጨረሻ ቀን ውሎው ለ2019 በጀት ዓመት 25 ቢሊዮን 424 ሚሊዮን 655 ሺህ 336 ብር በጀት ነው ያጸደቀው። የረቂቅ በጀቱን ዝርዝር ለምክር ቤቱ ያቀረቡት የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ዚያድ አብዱላሂ እንደገለፁት በጀቱ የክልሉን ገቢ የመሰብሰብ አቅም ያገናዘበ እና ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት የሚውል ነው ብለዋል። በጀቱ ለመሠረተ ልማት እና ለትልልቅ ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ ትኩረት የሰጠ መሆኑን ገልፀው፥ በየደረጃው የሚገኙ አስፈጻሚ አካላትም በጀቱን ለታለመለት ዓላማ ማዋል እንደሚጠበቅባቸው አስታውቀዋል። በክልሉ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱ እየተሻሻለ በመምጣቱ ከዘንድሮ በጀት 61 ነጥብ 5 በመቶ የሚሆነው በክልሉ የውስጥ ገቢ የሚሸፈን መሆኑን ኃላፊው ተናግረዋል። በረቂቅ በጀቱ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡ የምክርቤት አባላትም በጀቱን በቁጠባ እና በአግባቡ ተግባር ላይ በማዋል የህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን በፍትሃዊነት መፈጸም እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ምክርቤቱ በተጨማሪም የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልላዊ መንግስት የተሻሻለ የገቢ ግብር ለመወሰን የወጣ ረቂቅ አዋጅን እና የክልሉን የፋይናንስ አስተዳደርን ለማሻሻል የወጣ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ በማጽደቅ ጉባኤውን አጠናቋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን ከ133 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ እድል ተፈጥሯል
Jul 26, 2026 117
አምቦ ፤ ሐምሌ 19/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሸዋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ 133 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን የዞኑ የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ጽህፈት ቤት አስታወቀ። መንግስት በሀገሪቱ የሚታየውን የወጣቶች የሥራ አጥነት ቁጥር ለመቀነስ እና ዘላቂ የኢኮኖሚ እድገት ለማረጋገጥ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና የክህሎት ልማት ዘርፍን በትኩረት እየሰራበት ይገኛል። በተለይም በክልሎች በሚገኙ የተለያዩ ዞኖች የወጣቶችን አቅም በማሳደግ እና በየአካባቢው የሚገኙ የኢኮኖሚ አማራጮችን በማስፋት በርካቶች ወደ ሥራ እንዲገቡ እየተደረገ ይገኛል። በምዕራብ ሸዋ ዞንም በአካባቢው የሚገኙ የወጣቶችን የሥራ አጥነት ችግር ለማቃለል ባለፉት የበጀት ዓመታት በርካታ ስራዎች ሲከናወኑ ቆይተዋል። ዞኑ ለሥራ ዕድል ፈጠራ ምቹ የሆኑ የተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች ያሉት ሲሆን፣ ከነዚህም መካከል ግብርና እና የግብርና እሴት መጨመር፣ አነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች፣ የአገልግሎት ዘርፍ እና ንግድ ተጠቃሽ ናቸው። የምዕራብ ሸዋ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ የኔነሽ ምስጋና ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በ2018 በጀት ዓመት በዞኑ የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ አቅም ከማሳደግ ባለፈ በአገር እድገት ውስጥ የራሳቸውን ሚና እንዲወጡ ለማስቻል የተለያዩ ተግባራት ተከናውነዋል። በዚህም በዞኑ በከተማና በገጠር አካባቢዎች ለ129 ሺህ 132 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ፣ ከ133 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ተናግረዋል። የስራ እድሉ የተፈጠረው፣ በግብርና፣ በአገልግሎት፤ በእንጨትና ብረታ ብረት፤ የወተት ላምና የዶሮ እርባታ፣ የከብቶች ማድለብን ጨምሮ ሌሎች የሥራ ዘርፎች መሆናቸውን ገልፀዋል። ወጣቶቹ በሥራቸው ስኬታማ እንዲሆኑም የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠናዎችን ከመስጠት ባለፈ የብድር አቅርቦት፣ የመሥሪያና የመሸጫ ቦታዎች የማመቻቸት ስራዎች መሰራታቸውን ተናግረዋል። በዚህ መሰረት በማህበር ለተደራጁ ወጣቶች 1 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ብድር፣ ከ218 በላይ ሼዶችና ኮንቴይነሮች፣ 140 የሥራ ዘርፍ ክላስተሮች እንዲሁም 5 ሺህ 903 ሄክታር መሬት መቅረቡን ጠቁመዋል። ይህንን ተግባር አጠናክሮ በማስቀጠል በአዲሱ በጀት ዓመትም በርካታ ወጣቶችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ አዳዲስ የሥራ ዘርፎችን ለመፍጠር አቅደው እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ የሥራ እድል የተፈጠረላቸው ወጣቶች በበኩላቸው፤ ከመንግስት የተመቻቸላቸውን የብድር ድጋፍ እና የመስሪያ ቦታ በመጠቀም፣ በትጋትና በጥንካሬ በመስራት አሁን ላይ አርአያ የሚሆን ውጤት በማስመዝገብ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። ወጣት ጫላ አያና፤ በቶኬ ኩታዬ ወረዳ 'የጫላና ብርቱካን የእንጨትና ብረታ ብረት ስራ' በተሰኘው ማህበር በመደራጀት ከመንግስት ባገኙት 200 ሺህ ብርና ቦታ ተግተው በመስራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግሯል። በስራው የስራ እድል መፍጠር መቻላቸውን ጠቅሶ፣ እንዲሁም 100 ሺህ ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘታቸውን አክሏል። ሌላው ወጣት አብዲ ተስፋዬ እንደገለጸው፤ በተመቻቸላቸው ዕድል በመጠቀም ባገኙት 2 ሚሊዮን ብር ካፒታል መነሻነት ከጓደኞቹ ጋር በመደራጀት በወተት ላም እርባታ ላይ ተሰማርተው እየሰሩ ነው። ሥራውን በ10 ላሞች እንደጀመሩና በዚህም የራሳቸውንም ሆነ የቤተሰቦቻቸውን ሕይወት በተሻለ ሁኔታ እየመሩ እንደሚገኙ ተናግሯል። ከዩኒቨርሲቲ በድግሪ ከተመረቀ በኋላ ለሁለት ዓመታት ያለ ምንም ስራ ቤተሰቦቹ ላይ ጥገኛ ሆኖ መቆየቱን አስታውሶ፣ በአሁኑ ወቅት መንግስት ባመቻቸላቸው ምቹ ሁኔታን በመጠቀም ተደራጅቶ በመስራቱ ከራሱም አልፎ በኢኮኖሚው እድገት ውስጥ የራሱን ሚና ለመወጣት ማቀዱን አመልክቷል። በ'ብርሃኑ ኩማላ እና ጎደኞቹ' በተሰኘው ማህበር በዶሮ እርባታ በመደራጀት በተሰጣቸው 300ሺህ ብር ብድር 800 እንቁላል ጣይ ዶሮዎችን በማስገባት ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን የተናገረው ደግሞ ወጣት ሱፋና አለሙ ነው፡፡
የቡና ጥራትና ምርታማነትን ለማሻሻል የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jul 25, 2026 347
እምድብር፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ):- የቡና ጥራትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን አስታወቀ፡፡ የባለስልጣኑ ሰራተኞች የቡና ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር በጉራጌ ዞን በእምድብር ከተማ በሰሜ ቀበሌ አካሄደዋል ። የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን የዋና ዳይሬክተር ፅህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሰፊሳ አባቡ በወቅቱ እንደገለፁት የቡና ጥራትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው፡፡ ለዘርፉ በተሰጠው ልዩ ትኩረት የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ተደራሽ በማድረግ ምርትና ምርታማነት ወደ ላቀ ደረጃ ማድረስ መቻሉን ተናግረዋል። በዘርፉ በቅንጅት በተሰራው ስራ በቡና ምርታማነት ላይ የተገኘው ውጤት ተጠናክሮ እንዲቀጥል ይሰራል ብለዋል፡፡ የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቡናና ቅመማቅመም ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ቶፊቅ ጁሃር የቡና ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በተሰጠው ትኩረት ስኬት እየተመዘገበ ነው ብለዋል። በዘንድሮ አመት በክልሉ 48 ሚሊዮን ችግኝ የመትከል ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በሽታ የሚቋቋሙ፣ በአጭር ጊዜ የሚደርሱና ምርታማ የሆኑ ዝርያቸው የተሻሻሉ የቡና ችግኞች ለአርሶ አደሩ እየቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በብልፅግና ፓርቲ የጉራጌ ዞን ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ደሳለኝ ፈቀደ የቡና ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በቅንጅት ይሰራል ብለዋል። ወጣቶች ቡና በስፋት እና በጥራት በማምረት እንዲሁም በፍራፍሬ ልማት ላይ እንዲሳተፉ መደረጉን ያነሱት ደግሞ የእምድብር ከተማ ከንቲባ አቶ ግንባሩ በርጋ ናቸው ። የከተማው ወጣት ዳዊት ትእዛዙ በ4 ሄክታር መሬት ላይ ዝርያቸው የተሻሻሉ የቡና ችግኞች እያለማ መሆኑን ተናግሮ ዘንድሮም ይህን በማስፋት ከ2 ሺህ በላይ ችግኝ መትከሉን ተናግሯል፡፡ ሌላው በእምድብር ከተማ በቡና ልማት የተሰማሩት አቶ ሳሙኤል ፍራንሷ በበኩላቸው ባላቸው 3 ሄክታር ማሳ ላይ ቡና እያለሙ መሆኑን ጠቁመው ዘንድሮ ከ1 ሺህ በላይ የተሻሻለ የቡና ችግኝ መትከላቸውን ገልጸዋል፡፡
በብሄረሰብ አስተዳደሩ 34 የመስኖ ፕሮጀክቶች ተገንብተው ለአገልግሎት በቅተዋል
Jul 25, 2026 271
ሰቆጣ፤ ሃምሌ 18/2018(ኢዜአ)፡- በዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 34 የመስኖ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን የአስተዳደሩ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ ለኢዜአ እንደገለፁት አካባቢው ዝናብ አጠር በመሆኑ የመስኖ ፕሮጀክቶችን በስፋት በመገንባት ማሕበረሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም ከ539 ሚሊዮን ብር በላይ ወጭ 34 የመስኖ ፕሮጀክቶችን በመገንባት ለአገልግሎት ማብቃት መቻሉን ገልጸዋል። የተገነቡት የመስኖ ፕሮጀክቶችም 820 ሄክታር መሬት በማልማት ከአራት ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችሉ መሆናቸውን አስገንዝበዋል። ፕሮጀክቶቹ በብሄረሰብ አስተዳደሩ በበጋ ወቅት ጭምር በማምረት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውንም አመልክተዋል። ስራ የጀመሩት ፕሮጀክቶች አርሶ አደሩ በዓመት ከሁለት ጊዜ በላይ አትክልትና ፍራፍሬ ጨምሮ እንዲያመርትና የስርዓተ ምግብ ችግር እንዲያቃልል የሚያደርግ መሆናቸውንም ጨምረው ገልፀዋል። የሰቆጣ ከተማ የ03 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ንጉሱ አመረ እንዳሉት፤ በአካባቢያቸው የተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት ከዝናብ ጥገኝነት በመውጣት በዓመት እስከ ሶስት ጊዜ የማምረት አቅም እንድናገኝ የሚያደርግ ነው ። የጓሮ አትክልትና ፍሬፍሬ እንዲሁም ሌሎች የሰብል ምርቶችን በማሳደግ አኗኗራቸውን ለመቀየር የሚያስችላቸው መሆኑንም ጨምረው ገልፀዋል። በአስተዳደሩ በጋዝጊብላ ወረዳ 03 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አገኘሁ ጌታሁን፤በቀበሌያቸው የተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት ተጠቃሚ ያደረጋቸው መሆኑን ተናግረዋል። የተገነባው የመስኖ ፕሮጀክት በክረምት ዝናብ ብቻ የተመሰረተውን የግብርና ስራ በዓመት እስከ ሶስት ጊዜ በማምረት ተጠቃሚነታችን እንድናሳድግ የሚያደርግ ነው ብለዋል። በብሄረሰብ አስተዳደሩ ባለፉት ዓመታት በተገነቡ የመስኖ ተቋማት አራት ሺህ 885 ሄክታር መሬት ማልማት መቻሉን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በሸገር ከተማ አርሶ አደሩን በመደገፍ ምርትና ምርታማነቱን እንዲያሳድግ ተደርጓል
Jul 25, 2026 138
ሸገር፣ ሐምሌ 18/2018 (ኢዜአ)፡-በሸገር ከተማ በተጠናቀቀው በጀት አመት አርሶ አደሩን በመደገፍ ምርትና ምርታማነቱን እንዲያሳድግ የተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የሸገር ከተማ የግብርና ልማት ክላስተር አስተባባሪ አቶ ግርማ ኃይሉ ገለጹ። የሸገር ከተማ የ2018 በጀት ዓመት የ4ኛው ሩብ ዓመት የክትትልና አስፈጻሚ አካላት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። አቶ ግርማ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ አርሶ አደሩ የሚያካሒደውን የእርሻ ስራ በሜካናይዜሽን በማገዝ እና የግብርና ግብዓቶችን በወቅቱ በማቅረብ ስኬታማ ስራዎችን ማከናወን ተችሏል። በ2017/18 የምርት ዘመን በከተማዋ 81 ሺህ 538 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት 3 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ማግኘት መቻሉን ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ በመስኖ ስንዴ ልማት ከ42 ሺህ 613 ሄክታር መሬት በማረስ 2 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል ምርት መገኘቱንም አክለዋል። በተያዘው የመኸር የምርት ዘመንም 95 ሺህ 500 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። በተለይም የግብርና ሜካናይዜሽንን በማሳደግ ምርታማነትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ተግባራት ከፍተኛ ለውጥ ማምጣት መቻሉንም ነው የገለጹት። ከዚህ በተጨማሪ የከተማው አርሶ አደር የክረምቱን ዝናብ ብቻ ከመጠበቅ ወጥቶ በሁሉም ወቅቶች ማምረት እንዲችል የተለያዩ ጥረቶች መደረጋቸውንም ገልፀዋል። ለዚህም 171 ሚሊዮን ሜትር ኩብ የመስኖ ውኃ በማቅረብ 42 ሺህ 613 ሄክታር መሬት ማልማት መቻሉን ነው የተናገሩት።
በሸገር ከተማ በ2018 በጀት ዓመት በተከናወኑት የተለያዩ የልማት ስራዎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል
Jul 25, 2026 140
ሸገር፣ ሐምሌ 18/2018 (ኢዜአ)፡-በሸገር ከተማ ማሕበረሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ በ2018 በጀት ዓመት የተከናወኑ የልማት ስራዎች ስኬታማ መሆናቸውን የከተማዋ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር )ገለጹ። የሸገር ከተማ የ2018 በጀት ዓመት የ4ኛው ሩብ ዓመት የክትትልና አስፈጻሚ አካላት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። የከተማዋ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር ) ሪፖርቱንት ባቀረቡበት ወቅት እንዳሉት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የከተማዋንና የማሕበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ ተግባራትን በማከናወን ከፍተኛ ውጤት ተመዝግቧል። በተለይም የገቢ አቅምን ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት ከፍተኛ ለውጥ መምጣቱን አንስተው፣ በ2018 በጀት ዓመት 40 ነጥብ 17 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰብ መቻሉን አስረድተዋል። የተሰበሰበው ገቢ መሰረተ ልማቶችን በማስፋፋት ለማኅበረሰቡ የሚሰጠውን አገልግሎት ፈጣን፣ ተወዳዳሪና ዘመናዊ ለማድረግ የሚያስችል እንደሆነም ተናግረዋል። የተገኘው ገቢ ከአምው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ15 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ብልጫ ያለው መሆኑንም ነው የጠቆሙት። በበጀት ዓመቱ 348 የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት በማድረግ የሕብረተሰቡን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ተችሏል ነው ያሉት ። በከተማዋ በትምህርት ዘርፍ የተተገበሩ ኢኒሼቲቮችም በትምህርት ቤቶች ቁጥር፣ በትምህርት ዕድልና ተደራሽነት ረገድ ከፍተኛ ውጤቶች ማስመዝገብ መቻሉን ነው የገለጹት። በዚሁ መሠረት 121 የቅድመ መደበኛ እና 15 የ1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች መገንባታቸውን ነው ያመለከቱት። ከዚህ በተጨማሪ የተማሪዎች ምገባ መርሃ ግብርም በ1 ሺህ 224 ትምህርት ቤቶች ውስጥ ተግባራዊ ሆነዋል፤በዚህም 382 ሺህ 176 ተማሪዎችን ተጠቃሚ ማድረግ የተቻለ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም የተማሪዎችን መጠነ መቅረት ከማስቀረቱ ባለፈ የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ማገዙን አንስተዋል። በሸገር ከተማም የጤና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራትም ሶስት የሚደርሱ ሆስፒታሎችን አገልግሎት ማስጀመር መቻሉ አክለዋል። በሕብረተሰብ አቀፍ የጤና መድህን በኩልም ከአንድ ሚሊዮን በላይ የቤተሰብ አባላትን ማቀፍ የተቻለ ሲሆን 609 ሺህ በላይ ዜጎች የሕክምና አገለግሎት ማግኘታቸውንም ነው የተናገሩት። በተጠናቀቀው በበጀት ዓመት ንጹህ የመጠጥ ውሃን ተደራሽ በማድረግ 59 ነጥብ 9 በመቶ የነበረውን ሽፋን ወደ 71 በመቶ ለማሳደግ ተችሏል ነው ያሉት። በዚህም 322 ሺህ በላይ የሚደርስ ሕዝብ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። በሸገር ከተማ በ2018 በጀት ዓመት በመጀመሪያ ደረጃ እና በይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤቶች 8 ሺህ በላይ መዝገቦች እልባት አግኝተዋል ብለዋል።
በጅማ ዞን የፍራፍሬ ምርትን ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት ተገኝቷል
Jul 25, 2026 108
ጅማ፤ሐምሌ 18/2018 (ኢዜአ) ፡-በጅማ ዞን የፍራፍሬ ምርትን ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት ውጤት መገኘቱን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። ከዞኑ ለውጭ ገበያ የሚላክ ተጨማሪ የአቦካዶና ሙዝ ምርት የማጓጓዝ ስራ ዛሬ ተካሂዷል። የጅማ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ቲጃኒ ናስር እንደገለጹት በዞኑ ያለውን መሬትና የውሀ ሀብት በመጠቀም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው። አርሶ አደሩን በመደገፍና ቴክኖሎጂን በመጠቀም እንደ ቡና ሁሉ የፍራፍሬ ምርትን ለማሳደግ በተከናወነ ስራ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል ። በተለይም ባለፉት ስድስት አመታት የተሻሻሉ የሙዝና የአቦካዶ ዝርያዎችን በማስፋፋት ምርቱን በስፋት ለገበያ ማቅረብ መቻሉን ተናግረዋል። ከዞኑ በተጠናቀቀው በጀት አመት 6 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኪሎግራም የአቦካዶ እና ሙዝ ምርት ለገበያ መቅረቡን ጠቁመው ከዚህ ውስጥ 220 ሺህ ኪሎግራሙ ለውጭ ገበያ የቀረበ መሆኑን አስታውቀዋል ። በፍራፍሬ ልማቱ ህብረተሰቡ ተጠቃሚ ሆኗል ያሉት አቶ ቲጃኒ በተለይም ወጣቶች በዘርፉ ተደራጅተው ትርፋማ እየሆኑ መምጣታቸውን አመልክተዋል። የጅማ ዞን ግብርና ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም በበኩላቸው አርሶ አደሩ እየቀረበ ባለው የተሻሻለ የፍራፍሬ ዝርያ እና ሞያዊ ድጋፍ ምርቱ እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል ። የጅማ ዞን ቀርሳ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሀሰን መሀመድ በሚደረግልን ሞያዊ ድጋፍ አቦካዶን በማምረት ከ2014 ዓ. ም ጀምሮ ለዉጪ ገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ሆኛለሁ ብለዋል።
በዞኑ ለመኸር እርሻ የሚውል ከአንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ዘመናዊ የአፈር ማዳበሪያ እየተሰራጨ ነው
Jul 25, 2026 95
ምስራቅ ጎጃም፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ)፡-በምስራቅ ጎጃም ዞን ለመኸር እርሻ የሚውል ከአንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ዘመናዊ የአፈር ማዳበሪያ እየተሰራጨ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ምክትል ኃላፊ አቶ ጥላሁን ንጋቱ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በዘንድሮው ዓመት የመኸር ወቅት ማዳበሪያን ጨምሮ የተለያዮ ግብአቶች ጥቅም ላይ እንዲውሉ በማድረግ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል። ለዚህም ከአንድ ነጥብ አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ወደ ዞኑ በማስገባት የስርጭት ስራ መጀመሩን ነው የገለጹት። ወደ ዞኑ ከገባው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥም ከ980 ሺህ ኩንታል በላይ የሚሆነው ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የተደረገ ሲሆን ቀሪው በስርጭት ላይ እንደሆነም ነው የገለጹት። የማዳበሪያ አቅርቦቱ ምርታማነትን በማሳደግ ለኢንዱስትሪ ግብአትና ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት የራሱ የሆነ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አስገንዝበዋል። በዞኑ የጎዛምን ወረዳ የጥጃን ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አያሌው ክፋሌ ፤ ለምርት ማሳደጊያ የሚሆን የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ መቅረቡ የዘር ስራችን በተገቢው መንገድ ለማከናወነ አስችሎናል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅትም አራት ኩንታል የሚሆን የአፈር ማዳበሪያ በመውሰድም የበቆሎና ስንዴ ሰብል መዝራታቸውን አስረድተዋል። የአነደድ ወረዳ የጉዳለማ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ላመስግን መለሰ በበኩላቸው፤የአፈር ማዳበሪያ ተጠቃሚ መሆናቸው ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እንደሚያግዛቸው ነው የተናገሩት። የተረከቡትን ከአምስት ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ በመጠቀም መሬታቸውን በተለያዩ ሰብሎች ለመሸፈን እየሰሩ እንደሚገኙም አስረድተዋል። በዞኑ በ2018/2019 የምርት ዘመን በዘር ከሚሸፈነው ማሳ ከ26 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑ ተጠቁሟል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ለ2019 በጀት አመት 85 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር በጀት አጸደቀ
Jul 25, 2026 96
አርባምንጭ፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ)፦ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ለ2019 በጀት አመት 85 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር በጀት አጽድቋል። የክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 7ኛ መደበኛ ጉባኤውን በአርባምንጭ ከተማ እያካሄደ ነው። የክልሉ ፕላን፣ መሠረተ ልማትና የመንግስት ሀብት አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዕንቁ ዮሐንስ የክልሉ የ2019 ረቂቅ በጀት 85 ቢሊየን 774 ሚሊየን 12 ሺህ 25 ብር መሆኑን ለጉባኤው በዝርዝር አቅርበዋል። በጀቱ ከክልሉ በሚሰበሰብ ገቢና በፌደራል መንግስት ድጋፍ የሚሸፈን መሆኑን ተናግረዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ ተፈሪ አባተ በጀቱ በክልሉ ፍትሃዊ ልማት በማረጋገጥ የህብረተሰቡን አዳጊ ፊላጎት ለመመለስ ያለመ መሆኑን አብራርተዋል። በጀቱ በተለይም በድህነት ቀናሽ ዘርፎች ላይ ትኩረት ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም ተቋማት ለስራ ምቹ እንዲሆኑ የማደራጀትና ወቅቱ የደረሰበትን የዲጂታል ቴክኖሎጂ በመጠቀም ሁለንተናዊ የልማት ትልሞችን ለማሳካት ትኩረት መደረጉንም አመልክተዋል። በኢኮኖሚው መዋቅራዊ ሽግግር ለማምጣት የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ምርትና ምርታማነትን ለማላቅ፣ በሜካናይዜሽን በመታገዝ የግብርና ክፍለ ኢኮኖሚ ለማሳደግ ብሎም ለመሠረተ ልማት፣ ለትምህርት እና ለጤና ልማት አጽንኦት መሰጠቱን አስታውቀዋል። የምክር ቤቱ አባላት በቀረበው ረቂቅ በጀት ዙሪያ ውይይት በማድረግ አጽድቀዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ የተመዘገቡ ስኬቶች የክልሉን የመልማት አቅም ያረጋገጡ ናቸው - ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን
Jul 25, 2026 177
አሶሳ፤ ሐምሌ 18/2018 (ኢዜአ)፡- በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ የተመዘገቡ ስኬቶች የክልሉን የመልማት አቅም ያረጋገጡ መሆናቸውን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ገለጹ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5 ዓመት 3ኛ የሥራ ዘመን 5ኛ መደበኛ ጉባኤውን ማካሄድ ጀምሯል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን የተጠናቀቀው በጀት ዓመት አፈጻጸም ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት እንደገለፁት፤ በበጀት ዓመቱ ክልሉ በሁሉም ዘርፎች የተከናወኑ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ውጤታማ ናቸው። በዋናነት የክልሉ የኢኮኖሚ ምሰሶ የሆነውን የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት በቤተሰብ ደረጃ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ያረጋገጠ ሲሆን የኢኮኖሚ አቅሙንም ማሳደግ አስችሏል ብለዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም ከ55 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን አመልክተው የመካናይዜሽን እርሻ ተግባራዊ በመደረጉ ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን ጠቅሰዋል። በዚህም በሄክታር እስከ 34 ኩንታል ምርት ማግኝት ተችሏል ነው ያሉት በሪፖርታቸው። በተጨማሪም ባለፉት ጥቂት ዓመታት መንግስት ለማዕድን ዘርፉ ትኩረት መስጠቱ ለክልሉ ተጨማሪ የኢኮኖሚ ምንጭ ከመሆኑ ባለፈ ለሥራ ዕድል ፈጠራ ሰፊ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። ለአብነትም በበጀት ዓመቱ ዘርፉ ህጋዊ በሆነ መንገድ እንዲመራ በማድረግና አነስተኛ የማዕድን አምራቾችን ወደ ስራ በማስገባት ከ8 ሺህ 900 ኪሎግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ማቅረብ መቻሉን አስታውቀዋል። በክልሉ ያለውን የልማት ፍላጎት በራስ አቅም ለመሸፈን ለማድረግም የገቢ አሰባሰብ ሂደቱን በማዘመን የተሻለ ገቢ መሰብሰብ መቻሉን አመላክተዋል። በአጠቃላይ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተመዘገቡ ስኬቶች የክልሉን የመልማት አቅም ያረጋገጡና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያሳደጉ መሆናቸውን ርዕሰ መስተዳድሩ በሪፖርታቸው ገልጸዋል።
በከሚሴ ከተማ የተገነባው የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከማስዋብ የንግድ እንቅስቃሴን አነቃቅቷል
Jul 25, 2026 125
ደሴ፤ ሐምሌ 18/2018(ኢዜአ)፦ በከሚሴ ከተማ የተገነባው የኮሪደር ልማት ለከተማዋ ውበት ከመፍጠር ባሻገር የንግድ እንቅስቃሴ እንዲነቃቃ ማስቻሉን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለፁ። በከሚሴ ከተማ በንግድ ስራ የተሰማሩት አቶ አህመድ ጁሃር ለአዜአ እንደገለጹት፣ የተገነባው የኮሪደር ልማት ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ከመፍጠሩ ባሻገር፤ ለኢንቨስትመንት፣ ለንግድና ለነዋሪዎቿ የተመቸች እንድትሆን አድርጓል። የኮሪደር ልማቱ ለረጅም ጊዜ ሲነሱ የነበሩ የሕዝብ ጥያቄዎች የመለሰ በመሆኑ ቀጣይነት ያለውና ውጤታማ እንዲሆን በገንዘባችንና በጉልበታችን ተሳትፎ እናደርጋለን ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በተለያየ መስክ የተጀመሩ የልማት ስራዎች ቀጣይ እንዲሆኑም ከመንግስት ጎን ተሰልፈን ሰላማችንን በመጠበቅ የዜግነት ግዴታችን እንወጣለን ነው ያሉት። ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ ጣይቱ አሰፋ በበኩላቸው በከተማዋ ስንፈልገው የነበረ ልማት ተግባራዊ በመደረጉ ተጠቃሚ ሆነናል ሲሉ ገልጸዋል። የኮሪደር ልማቱ በተለይ የቆሻሻ መጣያ የነበሩና ለአይን የማይማርኩ ስፍራዎችን በማስዋብ ለእንቅስቃሴና ለመዝናኛ ምቹ ማድረግ በመቻሉ የከተማዋ ገጽታ መቀየሩን ተናግረዋል። የከሚሴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሸሪፍ ቃሲም በበኩላቸው፣ የከተማውን ሰላም ከማስጠበቅ ጎን ለጎን ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ልማቶች እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በልማቱ የተሽከርካሪ፣ የብስክሌትና የእግረኛ መንገድ ተለይቶ ከመሰራቱ ባለፈ የአረንጓዴ ሥፍራዎችና የህዝብ መዝናኛዎችን አካቶ መገንባቱን ነው የገለጹት።
የኮሪደር ልማት ትሩፋቶች፤ የከተሞች ህዳሴ
Jul 25, 2026 188
በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች የተጀመረው ሰፊ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት የመንገድ ጥገና ወይም የማስዋብ ስራ ብቻ ሳይሆን፤ የከተሞች አወቃቀር፣ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እና የማህበራዊ ህይወት ገጽታ ሙሉ በሙሉ የለወጠ ሥር ነቀል ከተማን የማደስ ትልቅ ስራ ነው። የከተማ እና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር ይፋ ባደረገው መረጃ መሠረት፣ በአሁኑ ወቅት የኮሪደር ልማቱ በአዲስ አበባ ከተገኘው ስኬት በመነሳት ወደ 75 በሚጠጉ የሀገሪቱ ዋና ዋና ከተሞችና ታዳጊ ከተሞች ተስፋፍቷል። ይህም ሀገሪቱ ከተበታተነና ጥራት ከጎደለው የመሰረተ ልማት አሰራር ወጥታ ወደ ዘመናዊና የተቀናጀ የከተሜነት ምዕራፍ መሸጋገሯን ያመላክታል። የኮሪደር ልማቱ ከዚህ ቀደም የነበሩ የከተሞች መዋቅራዊ ችግሮችን በጥቅሉ የፈታ ሲሆን፤ ዋና ዋናዎቹ የለውጥ መስኮች በሚከተሉት ነጥቦች ይጠቃለላሉ። አካታች የመንገድና የትራፊክ ፍሰት ቀደም ሲል መንገዶች ለባለሞተር ተሽከርካሪዎች ብቻ ያደሉ በመሆናቸው ለትራፊክ መጨናነቅና ለሚከሰቱ አደጋዎች ምክንያት ሆነው ቆይተዋል። የኮሪደር ልማቱ ሰፊ የእግረኛ፣ የብስክሌትና የስፖርት ማሳለጫ መንገዶችን፣ አየር ላይና ከመሬት በታች ድልድዮችን እንዲሁም ዘመናዊ የታክሲና አውቶቡስ ማቆሚያዎችን አካቶ ተገንብቷል። የተቀናጀ የመሬት ውስጥ የመሰረተ ልማት ዝርጋታ ተደጋጋሚ የመንገድ ቁፋሮዎችንና ብክነትን ለማስቀረት የውሃ፣ የኤሌትሪክ ኃይል፣ የቴሌኮም እና የፍሳሽ መስመሮች በመሬት ሥር እንዲያልፉ ተደርጓል። ይህም ከተሞችን በአየር ከተንጠለጠሉ ገመዶች ነፃ እያደረገ ይገኛል። በተጨማሪም በክረምት ወቅት የሚከሰተውን የጎርፍ አደጋ በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ እያስቻሉም ይገኛሉ። የ24 ሰዓት የኢኮኖሚ እንቅስቃሴና አረንጓዴ ሥፍራዎች፦ በኮሪደር ልማቱ ባዶና ቆሻሻ መጣያ የነበሩ ስፍራዎች ወደ አረንጓዴ መናፈሻዎችና የሕዝብ መዝናኛዎች ተቀይረዋል። ዘመናዊ የመንገድና የህንጻ መብራቶች መገጠማቸው ደግሞ የደህንነት ስሜትን በመጨመር የሌሊት የንግድ እንቅስቃሴ እንዲነቃቃ አድርጓል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኮሪደር ልማትን በተመለከተ ምን አሉ? ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እንደደገለጹት፣ የኮሪደር ልማቱ የመንገድ ግንባታ ብቻ ሳይሆን የሀገሪቱን የከተሞች ደረጃ የሚያሻሽልና የዜጎችን ሥነ-ልቦና የሚያንጽ ስትራቴጂያዊ ፕሮጀክት ነው። ኢትዮጵያ በታሪኳ ትልቅ ሀገር ነች፤ ስለዚህ ከተሞቻችንም ያንን ታላቅነታችንን የሚመጥን ፅዱ፣ አረንጓዴ እና ዘመናዊ ገጽታ ሊኖራቸው ይገባል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም የሀገር ግንባታ ቀጣይነት ያለው ሂደት መሆኑን በመግለጽ፣ ይህ ልማት ድህነትንና ቆሻሻን አለመቀበልን የሚያሳይ፣ ለቀጣይ ትውልድ የሚተላለፍ ኢትዮጵያን የመስራት ጉዞ አካል መሆኑንም ጠቁመዋል። በተጨማሪም በአዲስ አበባ የተገኘው ተሞክሮ ወደ አርባ ምንጭ፣ ባህር ዳር፣ አዳማ፣ ሀዋሳ እና ድሬዳዋ በመስፋፋቱ ፕሮጀክቱ በመላ ሀገሪቱ የሥራ ዕድል በመፍጠር በኩል ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ምሁራን በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ ሙሉ በሙሉ በመቀየር አዲስ ምዕራፍ የከፈተ መሆኑን ያነሳሉ። የከተማ ፕላንና ዲዛይን ባለሙያ ኢንጂነር አበበ ደሴ እንደሚሉት፤ የኮሪደር ልማቱ ለብዙ ዓመታት ሳይቀናጁ የዘለቁ እንደ የውሃ፣ የኤሌክትሪክ ሃይል፣ የቴሌኮም እና የፍሳሽ መስመሮች የመሳሰሉ የመሰረተ ልማት አውታሮችን በአንድ ላይ አቀናጅቶ በመሬት ሥር እንዲያልፉ ማድረጉ የከተሞችን እድሜ የሚያራዝምና አላስፈላጊ ተደጋጋሚ ቁፋሮዎችን ያስቀረ ትልቅ ሙያዊ እርምጃ ነው። የከተማ ልማትና አስተዳደር ምሁር በላይ አሰፋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማቱ የከተሞችን የቦታ አጠቃቀም ቅልጥፍና ያሻሻለ መሆኑን ይገልጻሉ። ቀደም ሲል ለቆሻሻ መጣያነትና ለሕገ-ወጥ ሥራዎች ይውሉ የነበሩ ቦታዎች ወደ ሕዝብ መናፈሻነትና አረንጓዴ ሥፍራነት መቀየራቸው የከተሞችን የሥነ-ምህዳር ሚዛን ለመጠበቅ እንደሚረዳ ነው የተናገሩት። የኢኮኖሚ ምሁሩ ቆስጠንጢኖስ በርኸ ተስፋ(ዶ/ር)፤ የኮሪደር ልማት በምሽት ጭምር ንግድ ማካሄድ የሚቻልበት አውድ የፈጠረ መሆኑን ይጠቅሳሉ። የከተሞች የኢኮኖሚ እንቅስቃሴን በማሳለጥ በኩል ዓይነተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል ነው ያሉት። ማጠቃለያ በአጠቃላይ፣ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት የኢትዮጵያን ከተሞች ከነበሩበት የተጨናነቀና ኋላቀር ገጽታ አውጥቶ ወደ ዘመናዊ፣ ፅዱ እና ለኢንቨስትመንት ሳቢ ወደሆኑ የከተማ ማዕከላት የመቀየር ትልቅ አዎንታዊ አስተዋጽኦ አበርክቷል። ይህም የኢትዮጵያን ገጽታ በመቀየር በአፍሪካም ተጠቃሽ ሀገር እያደረጋት ይገኛል፤ ከሥራ ዕድል ፈጠራ አኳያም የኮሪደር ልማት ሰፊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ከመሆኑም ባለፈ ፕሮክቶችን በአጭር ጊዜ ጀምሮ የመጨረስ ማሳያ ተደርጎም ይወሰዳል።
በሲዳማ ክልል በበልግ እርሻ ምርታማነትን የሚያሳድጉ ተግባራት ተከናውነዋል - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Jul 24, 2026 263
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በበልግ ወቅት እርሻ ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ተግባራት መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ፡፡ ርዕሰ መስተዳደሩን ጨምሮ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች በሀዋሳ ዙሪያ፣ በደራራ፣ በብላቴ ዙሪያ እና በዳሌ ወረዳዎች በበልግ የለማ ማሳ የመስክ ምልከታ አድርገዋል። ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በወቅቱ እንዳሉት በልግ አብቃይ በሆኑ አካባቢዎች በበቆሎ፣ ቦሎቄና ሌሎች ሰብሎች የለማው ማሳ በመልካም ሁኔታ ላይ ይገኛል። በምርት ወቅቱ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ለግብአት አጠቃቀምና ለግብርና ቴክኖሎጂ ትኩረት ተሰጥቶ መከናወኑን ጠቁመዋል። በበልግ እርሻው ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት በመኽር ወቅትም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ሀላፊ ታምሩ ሞኬ በበኩላቸው በክልሉ በበልግ እርሻ 152 ሺህ ሄክታር ማሳ በበቆሎ፣ ቦሎቄና ስራ ስር ሰብሎች መልማቱን ተናግረዋል። ከዚህ ውስጥ 67 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በበቆሎ መልማቱን ጠቁመው በምርት የተሸፈነውን ማሳ ውጤታማ ለማድረግም የእንክብካቤና የክትትል ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን አመልክተዋል፡፡ የሀዋሳ ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አለማየሁ ዲጋ በበኩላቸው አንድ ሄክታር ማሳ ላይ ያለሙት በቆሎ በመልካም ቁመና ላይ መሆኑን ተናግረዋል። ከግብርና ባለሙያ በሚሰጣቸው ምክር በመታገዝ እርጥበትን በማሳ ውስጥ እንዲቆይ በማድረጋቸው የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ አመላክተዋል። አርሶ አደር ጸሀይ በቀለ በበኩላቸው በማሳቸው ውስጥ እርጥበትን የማቆየት ስራ በመስራታቸው የበቆሎ ሰብላቸው በመልካም ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ኮርፖሬሽኑ ያደረገው ተቋማዊ ሪፎርም ለተከታታይ ዓመታት በውጤታማነት እንዲቀጥል አስችሎታል
Jul 24, 2026 271
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፦ ሁለንተናዊ ሀገራዊ ለውጡን መነሻ ያደረገው ተቋማዊ ሪፎርም ለተከታታይ ዓመታት ውጤታማነቱ እንዲረጋገጥ እንዳስቻለው የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ገለፀ። የኮርፖሬሽኑ በ2019 በጀት ዓመትም ይህንኑ አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያስችል ስትራቴጂካዊ አቅጣጫም ተቀምጧል። ኮርፖሬሽኑ የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ እና የ2019 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ ውይይቱን አካሂዷል። በዚህ የግምገማ መድረክ በበጀት ዓመቱ የተቀመጠውን ዕቅድ 97 በመቶ ማከናወን መቻሉ የተገለፀ ሲሆን፣ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በገቢ ዕድገት፣ በቤት ልማት፣ በመስፈጸም አቅም እና በቤት አስተዳደር ረገድ የተከናወኑት ሥራዎች የተቋሙን አጠቃላይ የለውጥ ጉዞ ማረጋገጣቸው ተጠቁሟል። በተጨማሪም የሕዝብና የመንግስት ጥቅም ለማስጠበቅ በፍርድ ቤት በተከናወኑ ክርክሮች በርካታ ይዞታዎችን ማስመለስ ተችሏል ብሏል። ኮርፖሬሽኑ በምሥራቅ አፍሪካ እና በአፍሪካ ገበያ ለመሰማራት ያስቀመጠውን ራዕይ ለማሳካት በሚያደርገው ጥረት፣ በደቡብ ሱዳን ጁባ ከተማ በቤት ልማት ለመሳተፍ ከደቡብ ሱዳን ኢኳቶሪያል ስቴት ጋር የተደረሰው ስምምነት ወደ ተግባር ለማስገባት ሥራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ አስታውቋል። የልማት ፕሮጀክቶችን በተመለከተ የፒያሳ እና የጎልድ ሳይት ፕሮጀክቶችን አጠናቆ ወደ አገልግሎት ማስገባት የተቻለ ሲሆን፣ ዘመናዊ የ3ዲ የግንባታ ቴክኖሎጂን ለማስፋፋት የሚያስችሉ የመጀመሪያዎቹ የሙከራ ቤቶች ግንባታም በመከናወን ላይ ይገኛሉ። በሌላ በኩል የቤቶች ቆጠራና የመረጃ ማሰባሰብ ሥራ በመጠናቀቁ ዘመናዊ የቤት አስተዳደር ሥርዓትን ማጠናከር የተቻለ ሲሆን፣ በርካታ የንግድ ቤቶችም ከደንበኞች ጋር በትብብር ተገንብተው ወደ ኪራይ አገልግሎት በመግባታቸው ከፍተኛ ገቢ ማስገኘት ጀምረዋል። ከዚህ ባሻገር የተቋሙን የ50 ዓመት የጉዞ ታሪክና ስኬቶች የሚያስተዋውቁ የተለያዩ መርሐግብሮች በኢዮቤልዩ በዓሉ ወቅት ለአራት ተከታታይ ቀናት በታላቅ ድምቀት ተከብረዋል። በዚህም የተቋሙን ገጽታ መቀየር መቻሉም ነው የተገለጸው፡፡ በአዲሱ የ2019 በጀት ዓመት ዘመናዊና ፈጣን የግንባታ ቴክኖሎጂዎችን በስፋት ሥራ ላይ ማዋል፣ የሀገር ውስጥ የቤት አቅርቦትን ለማሳደግ ሰፋፊ የቤት ልማት መርሐግብሮችን መተግበር፣ አዳዲስ አሰራሮችን በመጠቀም የገቢ ምንጮችንና የፋይናንስ አማራጮችን ማስፋፋት እንዲሁም የሰው ኃይል እና የአሰራር ሥርዓት አቅምን ማጠናከር ዋነኛ ስትራቴጂካዊ የትኩረት አቅጣጫዎች ሆነው ተቀምጠዋል። ኮርፖሬሽኑ በአዲሱ የበጀት ዓመት የግንባታ ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት ለአገራዊ የቤት ልማት ዕቅድ ስኬት በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አስታውቋል።
በሀረሪ ክልል በበጀት ዓመቱ 6 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዷል
Jul 24, 2026 126
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ የሀረሪ ክልል ገቢዎች ቢሮ በተያዘው በጀት ዓመት 6 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን አስታወቀ። በክልሉ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የነዋሪዎችን የመሠረተ ልማትና የአገልግሎት አቅርቦት ጥያቄዎች ለመመለስ ትኩረት መሰጠቱም ተመላክቷል። የቢሮ ኃላፊው ያሲን አብዱላሂ እንደገለጹት በ2019 በጀት ዓመት የግብር ዘመን 6 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ከሐምሌ 1/2018 ጀምሮ ሥራው መጀመሩን ጠቅሰዋል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት የገቢ አሰባሰብ ሥራው በቴክኖሎጂ መታገዙ፣ የባለሙያዎች አቅም መገንባቱና የገቢ ምንጮችን ማስፋት በመቻሉ ገቢን ማሳደግ ተችሏልም ነው ያሉት፡፡ በተያዘው የግብር ዘመንም የተጨማሪ እሴት ታክስ ገቢን የማሳደግ፣ ከቅጥር የሚገኝ ገቢን እና የአከራይ ተከራይ ገቢን አሟጦ የመሰብሰብ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል፡፡ በክልሉ ካለፉት ሁለት ዓመታት ጀምሮ ከጥሬ ገንዘብ ንክኪ ነፃ የሆነ የገቢ አሰባሰብ ሥርዐት በመዘርጋት በባንክ የክፍያ ማረጋገጫ ብቻ ገቢ እየተሰበሰበ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ በክልሉ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የነዋሪዎችን የመሠረተ ልማትና የአገልግሎት አቅርቦት ጥያቄዎች ለመመለስ ትኩረት መሰጠቱንም አመልክተዋል። ከሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ እየተካሄደ ባለው የገቢ አሰባሰብ ሂደት ግብር ከፋዮች ግብራቸውን እየከፈሉ እንደሚገኙም አቶ ያሲን ጠቁመዋል፡፡ ደንበኛ ተኮር አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ጠቁመው ሊፈጠር የሚችለውን ጫና ለመቀነስና ለግብር ከፋዩ አማራጭ የአገልግሎት ጊዜ ለመስጠት ሲባልም በዚህ የግብር ወቅት በተወሰኑ ሠራተኞች እስከ ምሽቱ 2 ሰአት ድረስ አገልግሎት የሚሠጥ መሆኑን ገልፀዋል።
የተፈጥሮ ማዳበሪያን በመጠቀማችን ወጪን ከመቀነስ ባለፈ ምርታማነታችን እያሳደገልን ነው - አርሶ አደሮች
Jul 24, 2026 130
መቱ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በኢሉባቦር ዞን በቀያቸው አዘጋጅተው እየተጠቀሙ ያሉት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ወጪ ከመቀነስ ባለፈ ምርታማነታቸውን እያሳደገ መሆኑን የዞኑ አርሶ አደሮች ገለጹ። በኢሉአባቦር ዞን በበቾ ወረዳ የተፈጥሮ ማዳበሪያን በማምረት እየተጠቀሙ ካሉት አርሶ አደሮች መካከል ወይዘሮ አይናለም ጌታቸው አንዷ ናቸው። ወይዘሮ አይናለም እንዳሉት፣ በግብርና ባለሙያዎች እገዛ ከአካባቢያቸው በሚገኙ ተረፈ ምርቶችና ዕፅዋት የተፈጥሮ ማዳበሪያ በማዘጋጀት መጠቀማቸው ከዚህ በፊት ለዘመናዊ ማዳበሪያ ይወጣ የነበረውን ወጪ ከማስቀረቱ በላይ የምርት መጠንን ማሳደጉን ገልጸዋል። የዲዱ ወረዳ አርሶ አደሩ ገዳሙ አርፋሳ የተፈጥሮ ማዳበሪያን በማዘጋጀት ለእርሻ ሥራቸው እየተጠቀሙ መሆኑንና ከራሳቸው ፍጆታ አልፈው ለሌሎች በመሸጥ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንደሆናቸው ተናግረዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያው የመሬት ለምነትን ጠብቆ የሚያቆይ በመሆኑ፣ ምርታማነት ለዓመታት ቀጣይነት እንዲኖረው ያስችላል ብለዋል። በበቾ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ተስፋዬ ዲቤሳ እንደተናገሩት በወረዳው የምርትና ምርታማነት ዕድገትን ለማረጋገጥ አርሶ አደሮቹን ተጠቃሚ ለማድረግ በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዙሪያ በተሠራው ሥራ ውጤት እየመጣ ነው። የኢሉአባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ ዳኜ ፍቅሬ እንደገለጹት በዞኑ በምርት ዘመኑ ከ265 ሺህ ኩንታል በላይ ዘመናዊ ማዳበሪያና ከ11 ሚሊየን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ እየዋለ ነው። በዚህም የዞኑ አርሶ አደር ባለው መሬት ላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘጋጅቶ በመጠቀም ውጤታማ እየሆነ መምጣቱን አንስተው፣ ልምድም እያዳበሩ ነው ብለዋል። በወረዳዎቹ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማዘጋጃ ማዕከላት ተገንብተው ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመው ለአርሶ አደሮች እንዲደርስ መደረጉን ገልጸዋል።
ዩኒቨርሲቲው የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በምርጥ ዘር አቅርቦትና በእጽዋት በሽታ ቁጥጥር ላይ ሙያዊ ድጋፍ እያደረገ ነው
Jul 24, 2026 226
ሮቤ፤ ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፡- መደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በምርጥ ዘር አቅርቦትና በእጽዋት በሽታ ቁጥጥር ላይ ሙያዊ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን አስታወቀ። ዩኒቨርሲቲው በኩታገጠም አሰራር ለተደራጁ 120 አርሶ አደሮች የምርጥ ዘር ድጋፍ አድርጓል። በመርሐግብሩ የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ፣ የምርምርና የቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት በዛብህ ወንድሙ (ዶ/ር) እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በምርጥ ዘርና በእጽዋት በሽታ ቁጥጥር ላይ እየሰራ ነው። ለዚህም ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በምርምር ያወጣቸውን የተሻሻሉ የስንዴ ዝርያዎችና የግብርና አሰራሮችን ለአርሶ አደሩ እያስተዋወቀ መሆኑንም ጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው ከግብርና ምርምር ማዕከላት የተለቀቁ ምርጥ ዘሮችን በራሱና በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በማባዛት ለአርሶ አደሩ መልሶ እያሰራጨ መሆኑንም አመልክተዋል። ይህም የአርሶ አደሮች ምርታማነት ከአንድ ሄክታር እስከ 80 ኩንታል ስንዴ ማምረት እንዳስቻለ አንስተዋል። ዩኒቨርሲቲው የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ የጀመረውን ስራ በማስፋት ከባሌ፣ ምሥራቅ ባሌና ምዕራብ አርሲ በኩታገጠም ለሚሰሩ ለተመረጡ 240 ለሚበልጡ አርሶ አደሮች ድጋፍና ክትትል እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዛሬው ዕለትም ከባሌ ዞን ለተመረጡ 120 አርሶ አደሮች የስንዴ ምርጥ ዘር ድጋፍ መደረጉ የጥረቱ አካልና ቀጣይነት ያለው መሆኑንም አመልክተዋል። ዩኒቨርሲቲው አርሶ አደሩን በምርጥ ዘር አቅርቦትና ሌሎች የግብርና ድጋፎችን ከማድረግ በተጓዳኝ በእጽዋት በሽታ ቁጥጥር ላይ ተግባር ተኮር ሙያዊ ድጋፍ እየሰጠ መሆኑንም አመልክተዋል። ድጋፉ ከተደረገላቸው አርሶ አደሮች መካከል ሐጅ ሁሴን አህመድ እንዳሉት በስንዴ ሰብል ልማት የመሳተፍ ረጅም ዓመት ልምድ ቢኖራቸውም ከምርጥ ዘር አጠቃቀም ልምድ ማነስ ምክንያት ከ25 ኩንታል የማይበልጥ የስንዴ እንደሚያመርቱ አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት ዩኒቨርሲቲው ያደረገላቸው የስንዴ ምርጥ ዘር ድጋፍ ምርታማነታቸውን ማሳደግ እንደሚያግዛቸው ገልጸዋል። ዩኒቨርሲቲው ከምርጥ ዘር በተጓዳኝ በየጊዜው በሚያደርግላቸው ሙያዊ ድጋፍ ምርታማነታቸውን እንዳሳደገው የገለጹት ደግሞ ሌላው አርሶ አደር ሐጅ አማን ጎዳና ናቸው።
በክልሉ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፍ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት ተከናውነዋል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Jul 24, 2026 309
አርባ ምንጭ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ተናገሩ፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ እየተካሄደ ባለው የክልሉ ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት እንዳመለከቱት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፍ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት ተከናውነዋል፡፡ ከዚህ ውስጥም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ300 ሺህ በላይ ዜጎች በገጠርና በከተማ የስራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። የስራ ዕድል ለተፈጠረላቸው ዜጎችም የመስሪያ እና የመሸጫ ቦታ፣ የመነሻ ካፒታል፣ የገበያ ትስሰር እና የድጋፍና ክትትል ስራዎች መከናወናቸውን ነው የጠቀሱት፡፡ በቱሪዝም ዘርፉም ልዩ ትኩረት በመሰጠቱ ዘርፉ እየተነቃቃ መምጣቱን ጠቅሰው ክልሉን ከጎበኙ የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች ከ1 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልጸዋል። በበጀት አመቱ በክልሉ ያለውን የገቢ አማራጮች አሟጦ ለመሰብሰብ በተከናወነው ተግባር 32 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ ተችሏል ነው ያሉት። ከተሞችን ከማልማት አኳያም ለኑሮ ምቹ እና ጽዱ ለማድረግ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንና ከዚህም በ27 ከተሞች እየተገነባ ያለው የኮሪደር ልማት ስራን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ በሌላ በኩል በማህበራዊ ዘርፍም የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተው በትምህርትና በጤና የተከናወኑ ውጤታማ ተግባራትን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም በትምህርት ለትውልድ ንቅናቄ ከ768 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ሀብት በመሰብሰብ የትምህር ቤቶችን ደረጃ የማሻሻል፣ ግብዓቶችን የማሟላት፣ የመምህራንን አቅም የመገንባትና ሌሎች ስራዎች መከናወናቸውን አመላክተዋል፡፡ በጤናው ዘርፍ የመሰረተ ልማት ግንባታና እና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት የህብረተሰቡን እርካታ ማረጋገጥ ያስቻሉ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ የጤና አገልግሎት ፍትሐዊነትን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና ያለው የማህበረሰብ ጤና መድህን አባላት ቁጥር እየጨመረ የመጣ ሲሆን ከአንድ ሚሊየን በላይ አባላትን ማፍራት መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 7ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ የሚገኝ ሲሆን ምክር ቤት አባላት ርዕሰ መስተዳድሩ ባቀረቧቸው ሪፖርት ዙሪያ ውይይት በማድረግ ላይ ይገኛሉ።