ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የተፈጥሮ ማዳበሪያን በመጠቀማችን ወጪን ከመቀነስ ባለፈ ምርታማነታችን እያሳደገልን ነው - አርሶ አደሮች
Jul 24, 2026 33
መቱ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በኢሉባቦር ዞን በቀያቸው አዘጋጅተው እየተጠቀሙ ያሉት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ወጪ ከመቀነስ ባለፈ ምርታማነታቸውን እያሳደገ መሆኑን የዞኑ አርሶ አደሮች ገለጹ።   በኢሉአባቦር ዞን በበቾ ወረዳ የተፈጥሮ ማዳበሪያን በማምረት እየተጠቀሙ ካሉት አርሶ አደሮች መካከል ወይዘሮ አይናለም ጌታቸው አንዷ ናቸው። ወይዘሮ አይናለም እንዳሉት፣ በግብርና ባለሙያዎች እገዛ ከአካባቢያቸው በሚገኙ ተረፈ ምርቶችና ዕፅዋት የተፈጥሮ ማዳበሪያ በማዘጋጀት መጠቀማቸው ከዚህ በፊት ለዘመናዊ ማዳበሪያ ይወጣ የነበረውን ወጪ ከማስቀረቱ በላይ የምርት መጠንን ማሳደጉን ገልጸዋል።   የዲዱ ወረዳ አርሶ አደሩ ገዳሙ አርፋሳ የተፈጥሮ ማዳበሪያን በማዘጋጀት ለእርሻ ሥራቸው እየተጠቀሙ መሆኑንና ከራሳቸው ፍጆታ አልፈው ለሌሎች በመሸጥ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንደሆናቸው ተናግረዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያው የመሬት ለምነትን ጠብቆ የሚያቆይ በመሆኑ፣ ምርታማነት ለዓመታት ቀጣይነት እንዲኖረው ያስችላል ብለዋል።   በበቾ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ተስፋዬ ዲቤሳ እንደተናገሩት በወረዳው የምርትና ምርታማነት ዕድገትን ለማረጋገጥ አርሶ አደሮቹን ተጠቃሚ ለማድረግ በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዙሪያ በተሠራው ሥራ ውጤት እየመጣ ነው።   የኢሉአባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ ዳኜ ፍቅሬ እንደገለጹት በዞኑ በምርት ዘመኑ ከ265 ሺህ ኩንታል በላይ ዘመናዊ ማዳበሪያና ከ11 ሚሊየን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ እየዋለ ነው። በዚህም የዞኑ አርሶ አደር ባለው መሬት ላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘጋጅቶ በመጠቀም ውጤታማ እየሆነ መምጣቱን አንስተው፣ ልምድም እያዳበሩ ነው ብለዋል። በወረዳዎቹ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማዘጋጃ ማዕከላት ተገንብተው ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመው ለአርሶ አደሮች እንዲደርስ መደረጉን ገልጸዋል።
ዩኒቨርሲቲው የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በምርጥ ዘር አቅርቦትና በእጽዋት በሽታ ቁጥጥር ላይ ሙያዊ ድጋፍ እያደረገ ነው
Jul 24, 2026 106
ሮቤ፤ ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፡- መደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በምርጥ ዘር አቅርቦትና በእጽዋት በሽታ ቁጥጥር ላይ ሙያዊ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን አስታወቀ። ዩኒቨርሲቲው በኩታገጠም አሰራር ለተደራጁ 120 አርሶ አደሮች የምርጥ ዘር ድጋፍ አድርጓል። በመርሐግብሩ የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ፣ የምርምርና የቴክኖሎጂ ሽግግር ምክትል ፕሬዚዳንት በዛብህ ወንድሙ (ዶ/ር) እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በምርጥ ዘርና በእጽዋት በሽታ ቁጥጥር ላይ እየሰራ ነው።   ለዚህም ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር በምርምር ያወጣቸውን የተሻሻሉ የስንዴ ዝርያዎችና የግብርና አሰራሮችን ለአርሶ አደሩ እያስተዋወቀ መሆኑንም ጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው ከግብርና ምርምር ማዕከላት የተለቀቁ ምርጥ ዘሮችን በራሱና በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በማባዛት ለአርሶ አደሩ መልሶ እያሰራጨ መሆኑንም አመልክተዋል። ይህም የአርሶ አደሮች ምርታማነት ከአንድ ሄክታር እስከ 80 ኩንታል ስንዴ ማምረት እንዳስቻለ አንስተዋል። ዩኒቨርሲቲው የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ የጀመረውን ስራ በማስፋት ከባሌ፣ ምሥራቅ ባሌና ምዕራብ አርሲ በኩታገጠም ለሚሰሩ ለተመረጡ 240 ለሚበልጡ አርሶ አደሮች ድጋፍና ክትትል እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዛሬው ዕለትም ከባሌ ዞን ለተመረጡ 120 አርሶ አደሮች የስንዴ ምርጥ ዘር ድጋፍ መደረጉ የጥረቱ አካልና ቀጣይነት ያለው መሆኑንም አመልክተዋል። ዩኒቨርሲቲው አርሶ አደሩን በምርጥ ዘር አቅርቦትና ሌሎች የግብርና ድጋፎችን ከማድረግ በተጓዳኝ በእጽዋት በሽታ ቁጥጥር ላይ ተግባር ተኮር ሙያዊ ድጋፍ እየሰጠ መሆኑንም አመልክተዋል።   ድጋፉ ከተደረገላቸው አርሶ አደሮች መካከል ሐጅ ሁሴን አህመድ እንዳሉት በስንዴ ሰብል ልማት የመሳተፍ ረጅም ዓመት ልምድ ቢኖራቸውም ከምርጥ ዘር አጠቃቀም ልምድ ማነስ ምክንያት ከ25 ኩንታል የማይበልጥ የስንዴ እንደሚያመርቱ አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት ዩኒቨርሲቲው ያደረገላቸው የስንዴ ምርጥ ዘር ድጋፍ ምርታማነታቸውን ማሳደግ እንደሚያግዛቸው ገልጸዋል።   ዩኒቨርሲቲው ከምርጥ ዘር በተጓዳኝ በየጊዜው በሚያደርግላቸው ሙያዊ ድጋፍ ምርታማነታቸውን እንዳሳደገው የገለጹት ደግሞ ሌላው አርሶ አደር ሐጅ አማን ጎዳና ናቸው።
በክልሉ በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፍ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት ተከናውነዋል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Jul 24, 2026 83
አርባ ምንጭ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ተናገሩ፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ እየተካሄደ ባለው የክልሉ ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት እንዳመለከቱት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በኢኮኖሚና በማህበራዊ ዘርፍ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተግባራት ተከናውነዋል፡፡ ከዚህ ውስጥም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ300 ሺህ በላይ ዜጎች በገጠርና በከተማ የስራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። የስራ ዕድል ለተፈጠረላቸው ዜጎችም የመስሪያ እና የመሸጫ ቦታ፣ የመነሻ ካፒታል፣ የገበያ ትስሰር እና የድጋፍና ክትትል ስራዎች መከናወናቸውን ነው የጠቀሱት፡፡   በቱሪዝም ዘርፉም ልዩ ትኩረት በመሰጠቱ ዘርፉ እየተነቃቃ መምጣቱን ጠቅሰው ክልሉን ከጎበኙ የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች ከ1 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልጸዋል። በበጀት አመቱ በክልሉ ያለውን የገቢ አማራጮች አሟጦ ለመሰብሰብ በተከናወነው ተግባር 32 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ ተችሏል ነው ያሉት። ከተሞችን ከማልማት አኳያም ለኑሮ ምቹ እና ጽዱ ለማድረግ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንና ከዚህም በ27 ከተሞች እየተገነባ ያለው የኮሪደር ልማት ስራን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ በሌላ በኩል በማህበራዊ ዘርፍም የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተው በትምህርትና በጤና የተከናወኑ ውጤታማ ተግባራትን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም በትምህርት ለትውልድ ንቅናቄ ከ768 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ሀብት በመሰብሰብ የትምህር ቤቶችን ደረጃ የማሻሻል፣ ግብዓቶችን የማሟላት፣ የመምህራንን አቅም የመገንባትና ሌሎች ስራዎች መከናወናቸውን አመላክተዋል፡፡   በጤናው ዘርፍ የመሰረተ ልማት ግንባታና እና ቀልጣፋ አገልግሎት በመስጠት የህብረተሰቡን እርካታ ማረጋገጥ ያስቻሉ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ የጤና አገልግሎት ፍትሐዊነትን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና ያለው የማህበረሰብ ጤና መድህን አባላት ቁጥር እየጨመረ የመጣ ሲሆን ከአንድ ሚሊየን በላይ አባላትን ማፍራት መቻሉን ጠቅሰዋል፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 7ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ የሚገኝ ሲሆን ምክር ቤት አባላት ርዕሰ መስተዳድሩ ባቀረቧቸው ሪፖርት ዙሪያ ውይይት በማድረግ ላይ ይገኛሉ።
በቢዝነስ ዲፕሎማሲ የኢንቨስትመንት ዕድሎችን ማስፋትና የቱሪዝም ዘርፉን ከማነቃቃት አኳያ አመርቂ ሥራዎች ተሰርተዋል
Jul 24, 2026 93
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በቢዝነስ ዲፕሎማሲ ማዕቀፍ የኢንቨስትመንት ዕድሎችን ማስፋት፣ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን መሳብ እና የቱሪዝም ዘርፉን ከማነቃቃት አኳያ አመርቂ ሥራዎች መሰራታቸውን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄነራል አምባሳደር ዘሪሁን አበበ ገለጹ። መንግሥት በሀገሪቱ ምጣኔ ሀብታዊ እንቅስቃሴ ውስጥ ያሉ ማነቆዎችን በመፍታት ወደ ተሻለ እድገት ጎዳና ለመጓዝ ከወሰዳቸው እርምጃዎች መካከል ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ይጠቀሳል። እርምጃውም በሀገር ውስጥ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ የሚሳተፉ የሀገር ውስጥ ኢንቨስተሮችን ከመሳብ ባለፈ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን ከመሳብ አኳያ አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ ይገኛል፡፡ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄነራል አምባሳደር ዘሪሁን አበበ ለኢዜአ እንደገለጹት ኢትዮጵያ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን መሳብ የሚያስችል ምቹ መልከዓ ምድራዊና ኢኮኖሚያዊ አቅሞች ያላት ሀገር ናት፡፡ ነገር ግን ይህን ያላትን ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ ማዋል የሚያስችሉ የአሰራር ስርዓቶችን በመዘርጋት ለሀገር ሁለንተናዊ የልማት እድገት ከማዋል አንጻር ክፍተቶች እንደነበሩ ተናግረዋል። በሀገሪቱ ከዚህ ቀደም የነበሩ የፖሊሲ፣ የሕግና የፋይናንስ ማዕቀፎች ኢትዮጵያ ለውጭ ቀጥታ ኢንቨትመንት ምቹ አለመሆን እንደ ምክንያትነት አንስተዋል። መንግሥት ችግሩን ለመፍታት በወሰዳቸው ሀገር በቀል የማክሮ የኢኮኖሚ ማሻሻያና መዋቅራዊ ለውጦች የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን በሀገሪቱ እንዲነቃቃ አቅም ፈጥሯል ብለዋል። ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፍ ቢዝነስ ምቹ መደላድል መፍጠሯ የውጭ ባለሀብቶችና ድርጅቶች በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ ያላቸው ፍላጎት እንዲያድግና የኢንቨስትመንት ፍሰት እንዲጨምር ማድረጉን አስታውቀዋል። ከዚህም ባለፈ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ምክንያት ከተለመዱት የኢንቨስትመንት ምንጮች በተጨማሪ ከአፍሪካ፣ ከገልፍ እና ከእስያ ሀገራት አዳዲስ ኢንቨስተሮች በስፋት በሀገራችን ኢንቨስት እያደረጉ መሆኑ አንዱ ማሳያ ነው ሲሉ ገልጸዋል። ለአብነትም በናይጄሪያው ዳንጎቴ ኩባንያ በኩል በሲሚንቶ፣ በማዳበሪያና በሌሎች መስኮች ሰፊ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ በኢትዮጵያ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው የቴሌኮም ዘርፉም ለውጭ ኢንቨስትሮች ክፍት መደረጉን ተከተሎ የኬንያ ኩባንያዎች ወደ ሀገር ውስጥ መግባታቸውን አስታውቀዋል። ከተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፣ ከሳውዲ አረቢያ፣ ከኩዌት እና ቬይትናም የሚመጡ ባለሀብቶች በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩን አንስተው በቬይትናም ኩባንያ የሚከናወነው የሶላር ፓናል ማምረት ስራ ለሀገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እያስገኘ መሆኑንም አክለዋል። የቢሾፍቱ ኢንተርናሽናል ኤርፖርት ግንባታ መጀመሩ በርካታ ግዙፍ ተቋማት ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት እንዲያሳዩ በር መክፈቱንም አንስተዋል። አምባሳደር ዘሪሁን አያይዘውም መንግሥት የውጭ ቀጥታ ኢንቨትመንትን ለመሳብ የተጀመሩ ስራዎችን ለማስቀጥል ለንፋስ ኃይል፣ ለተፈጥሮ ጋዝ ልማት፣ ለፋርማሲዩቲካል፣ ለግብርና እና ለማምረ ዘርፎች ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ አብራርተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በገበታ ለሀገር ኢንሼቲቭ የተገነቡ የቱሪዝም መሰረተ ልማቶች እንዲሁም በቡና ምርት ላይ የመጡ መዋቅራዊ ለውጦች በርካታ ጎብኚዎችንና ኢንቨስተሮችን እየሳቡ አንደሚገኙ ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያን ከሀገር ውጭ ኢንቨስት በማድረግ ተጨማሪ የውጭ ምንዛሬ የሚያገኙበት አሰራር መዘርጋቱ ሀገሪቱ ያላትን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድግ መሆኑን አመልክተዋል። ሚኒስቴሩም ከቀደሙት ዋና ዋና ተልዕኮዎቹ መካከል የቢዝነስ ዲፕሎማሲ ግንባር ቀደሙ ነው ብለዋል። ተልዕኮውን እውን ለማድረግም የሀገሪቱን የኢንቨስትመንት እድሎች በማስተዋወቅ፣ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት በመሳብ፣ ለሀገር ውስጥ ምርቶች የውጭ ገበያ በማፈላለግና የቱሪዝም ዘርፉን በማሳደግ በኩል ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው ብለዋል። በዚህም ድርጅቶችና ግለሰቦች ሀገሪቱን እንዲጎበኙ ከማመቻቸት ጀምሮ፣ ጉብኝቱን ተከታትለው ኢንቨስት እንዲያደርጉ የማነሳሳትና የማግባባት ስራዎችን በከፍተኛ ደረጃ እየሰራ እንደሚገኝ በዚህም ተጨባጭ ለውጦች እየታዩ መሆኑ አመልክተዋል። በተጠናቀቀው 2018 በጀት ዓመት 4 ነጥብ 32 ቢሊየን ዶላር የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ወደ ሀገር ውስጥ መሳብ መቻሉን ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
በክልሉ በኮንስትራክሽንና የከተማ ግብርናን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች የስራ እድል የተፈጠረላቸው ዜጎች የብድር ተጠቃሚ ሆነዋል
Jul 24, 2026 70
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በኮንስትራክሽንና የከተማ ግብርናን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች የስራ እድል የተፈጠረላቸው ዜጎች የብድር ተጠቃሚ መሆናቸውን የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሥራ ዕድል ፈጠራና በባለሙያዎች ብቃት ምዘና ማረጋገጫ ተግባራት አፈጻጸም ላይ ያተኮረ መግለጫ ዛሬ ተሰጥቷል። የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አማረ ዓለሙ እንደገለጹት፤ ቢሮው በሰው ሀብት ልማት፣ በሥራ ዕድል ፈጠራና በኢንዱስትሪ ኤክስቴንሽን ድጋፍ ላይ በማተኮር ሲሰራ ቆይቷል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተከናወነው ቅንጅታዊ ስራ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊየን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል። የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ወገኖች መካከል ከ986 ሺህ 670 በላይ የሚሆኑት ቋሚ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ሲሆኑ፣ ቀሪዎቹ ደግሞ ጊዜያዊ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ናቸው። የሥራ ዕድሉን መፍጠር የተቻለውም በኮንስትራክሽን፣ በከተማ ግብርና፣ በአገልግሎት፣ በእንጨትና ብረታብረት ሥራ እና በሌሎች የዕድገት ተኮር ዘርፎች መሆኑን አመላክተዋል። ለሥራ ዕድል ተጠቃሚዎች 3 ቢሊየን ብር ብድር ለማቅረብ ታቅዶ ከእቅድ በላይ ከ10 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር በላይ ማሰራጨት ተችሏል ብለዋል። በዚህም የነበረባቸውን የመሥሪያ ገንዘብ ችግር ለመቅረፍ ተሞክሯል ያሉት ምክትል ኃላፊው የመሥሪያና የመሸጫ መሬት እንዲሁም ሼድ መስጠት መቻሉንም ጠቁመዋል። በበጀት ዓመቱ በተደረገው የተጠናከረ ድጋፍና ክትትል ከ15 ሺህ 700 በላይ ኢንተርፕራይዞች የደረጃ ሽግግር ማድረጋቸውን አብራርተዋል። የአማራ ክልል የሙያ ብቃትና ምዘና ማረጋገጫ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ተስፋዬ የሺዋስ በበኩላቸው፤ በበጀት ዓመቱ በመካከለኛ ደረጃ የሚገኙ ሙያተኞችን ብቃት ማረጋገጥ ላይ በማተኮር መሰራቱን ገልጸዋል። በዚህም በኮሌጆች በዲፕሎማ ደረጃ የሠለጠኑ ከ224 ሺህ በላይ ዜጎች የብቃት ምዘና እንዲወስዱ ተደርጎ፣ ከ70 በመቶ በላይ የሚሆኑት ምዘናውን በማለፍ የማረጋገጫ ሰርተፊኬት ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ይህም ለአምራች ኢንዱስትሪዎችና ለሌሎች የኢንቨስትመንት ዘርፎች ብቃት ያለው የሰው ሀብት በማቅረብ የተጀመረው ዕድገት ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሚያስችል መሆኑን አስገንዝበዋል።
በተያዘው የክረምት ወቅት ከ256 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Jul 24, 2026 100
ባህር ዳር ሃምሌ 17/2018;-በአዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን በተያዘው የክረምት ወቅት ከ256 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ አንዱዓለም አያሌው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተያዘው የመኸር ወቅት ምርት እና ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት እየተሰራ ነው። በአጠቃላይ በተያዘው መኸር የምርት ዘመንም 412 ሺህ 480 ሄክታር መሬት በዘር በመሸፈን ከ17 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ለማምረት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል። በመኸር እርሻው ከ187 ሺህ በላይ የዞኑ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ ሲሆን እስካሁን ባለው 256 ሺህ 249 ሄክታር መሬት በቆሎ ፣ ጤፍ ፣ ዳጉ ሳ፣ ስንዴ ፣ ሰሊጥ ፣ ሩዝ ፣ አኩሪ አተርና ሌሎች ሰብሎች በዘር መሸፈን ተችሏል። በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥም ከ169 ሺህ 790 ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም የተዘራ መሆኑን አስረድተዋል። በዞኑ ገበያ ተኮር የሆኑ የቅባት ሰብሎችን በማምረት ለኢንዱስትሪ ግብአትና ለገበያ ለማቅረብ እንዲቻል እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ምርታማነትን ለማሳደግም ለተያዘው እቅድ ስኬትም 484 ሺህ ኩንታል ማዳበሪያና ከ28 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ ማሰራጨት ተችሏል ብለዋል። የተሰራጨው የምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በዞኑ ባለፈው በጀት ዓመት በሔክታር የተገኝውን 41 ኩንታል ምርት ወደ 43 ነጥብ ስምንት በመቶ ለማሳደግ የሚያስቸል ነው ብለዋል። እቅዱን ሙሉ በሙሉ ለማሳካትም ከዞን እስከ ቀበሌ ያለው አመራርና ባለሙያ ለአርሶ አደሩ ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እያደረገ እንደሚገኝ አመላክተዋል።  
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የምግብ ሉዓላዊነትንና የኢንዱስትሪ ግብአትን መሰረት ያደረጉ የግብርና ልማት ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ ነው
Jul 24, 2026 104
አርባ ምንጭ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የምግብ ሉዓላዊነትንና የኢንዱስትሪ ግብአትን መሰረት ያደረጉ የግብርና ልማት ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ ውጤትም እየተመዘገበ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 7ኛ መደበኛ ጉባኤ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።   የክልሉን መንግሥት የ2018 በጀት ዓመት አጠቃላይ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ያቀረቡት ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ፤ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና የህዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ የልማት ኢንሼቲቮች እየተተገበሩ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በሌማት ትሩፋት፣ በስንዴ ልማት እና በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከተፈጥሮ ሃብት ልማት ባለፈ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ሂደት የተመዘገበውን ስኬት ለአብነት ጠቅሰዋል።   በመሆኑም የምግብ ሉዓላዊነትንና የኢንዱስትሪ ግብአትን መሰረት ያደረጉ የግብርና ልማት ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ ውጤትም እየተመዘገበባቸው ይገኛል ብለዋል። በቱሪዝም እና የማዕድን ሃብት ልማት፣ መስኖ ልማትና በኩታ ገጠም እርሻ፣ የሌማት ትሩፋት እንዲሁም የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት አስደናቂ ስኬት መመዝገቡን ጠቅሰዋል።
በሲዳማ ክልል በበልግ እርሻ ተዘርተው የደረሱ ሰብሎችን ውጤታማ ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jul 24, 2026 75
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 17/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በበልግ እርሻ ተዘርተው የደረሱ ሰብሎችን ውጤታማ ማድረግ የሚያስችሉ የእንክብካቤና የክትትል ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ አስታወቀ፡፡ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞን ጨምሮ የክልሉ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች በበልግ ወቅት በተለያዩ ሰብሎች የለሙ ማሳዎችን እየገበኙ ነው። በጉብኝቱ ወቅት የቢሮው ኃላፊ መምሩ ሞኬ እንዳሉት፤ በሲዳማ ክልል በበልግ እርሻ ተዘርተው የደረሱ ሰብሎችን ውጤታማ ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በክልሉ በበልግ እርሻ በቆሎ፣ ቦሎቄና ሌሎች ሰብሎችን ጨምሮ 152 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ ለምቷል ብለዋል፡፡ ከዚህም 24 ሚሊየን ኩንታል ምርት ይሰበሰባል ተብሎ እንደሚጠበቅ አመልክተው፤ በምርት የተሸፈነውን ማሳ ውጤታማ ለማድረግም የእንክብካቤና የክትትል ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን አመልክተዋል፡፡ በበልግ ወቅት የመስኖና ሌሎች አማራጮችን በመጠቀም የለማው ሰብል የሚጠበቀውን ምርት እንዲሰጥ እየተሰራ መሆኑንም ገልፀዋል፡፡
ምክር ቤቱ የህዝቡ የልማት ጥያቄዎች እንዲመለሱ ውጤታማ የክትትልና የቁጥጥር ስራ አከናውኗል
Jul 24, 2026 83
አርባምንጭ፤ ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፡- የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህዝቡ የልማት ጥያቄዎች እንዲመለሱ ውጤታማ የክትትልና የቁጥጥር ስራ ማከናወኑን ገለጸ፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 7ኛ መደበኛ ጉባኤውን በአርባምንጭ ከተማ እያካሄደ ነው።   የክልሉ ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባኤ ወላይቴ ቢቶ በጉባኤው መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ምክር ቤቱ የአስፈጻሚ አካላትን የስራ እንቅስቃሴ በመከታተልና በመቆጣጠር ውጤታማ ተግባር አከናውኗል። የአስፈጻሚ አካላት የልማት እንቅስቃሴን በቋሚ ኮሚቴዎች በማስገምገምና በመስክ ስራ ክትትልና ድጋፍ ጠንካራ ስራ መከናወኑን ጠቅሰዋል።   በበጀት ዓመቱ በክልሉ ሁለንተናዊ ዕድገት ለማስመዝገብ፣ የህዝቡን የልማት ፍላጎት እንዲሁም ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ጥያቄዎችን ለመመለስ ከፍተኛ ጥረት መደረጉን አንስተዋል ። በተለይም የህዝቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ እንዲመለሱ የተደረገ ጥረት ውጤታማ መሆኑን አመልክተዋል።    
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ከ118 ሺህ የሚበልጡ ዜጎች የስራ ዕድል ተጠቃሚ ሆነዋል
Jul 24, 2026 88
ጭሮ ፤ሐምሌ 17/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሐረርጌ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ118 ሺህ የሚበልጡ ዜጎችን የስራ እድል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የዞኑ ስራ ዕድል ፈጠራ ጽህፈት ቤት ገለፀ። የሥራ ዕድሉ ተጠቃሚዎችም በመንግሥት በተመቻቸላቸው የብድርና የማምረቻ ቦታ በመታገዝ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። የጽሕፈት ቤቱ የዕቅድ ዝግጅት እና ክትትል ቡድን መሪ አቶ አሸብር ደበበ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ ጽሕፈት ቤቱ በ8 ሺህ 801 ማኅበራት ለተደራጁ 118 ሺህ 500 ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩን አስረድተዋል። ለዚህም ስኬታማነት የመሬት ዝግጅት፣ የብድር አቅርቦትና የስልጠና አገልግሎት በመስጠት ዜጎችን ወደ ሥራ ማስገባት ተችሏል ብለዋል። ከተፈጠረው የሥራ መስክ መካከል ግብርና፣ የእንስሳት እርባታና ማድለብ፣ ንብ ማነብ፣ የዶሮ እርባታ፣ የጥቃቅንና አነስተኛ ንግድና ሌሎችም እንደሚገኙበት አመላክተዋል። በእንቅስቃሴያቸው ውጤታማ እንዲሆኑም በገጠርና በከተሞች በ3 ሺህ 200 ማኅበራት ለተደራጁ ወጣቶች 4 ሺህ 335 ሄክታር የእርሻና የመስሪያ ቦታ መሰጠቱን ጠቁመዋል። የመነሻ ካፒታል እጥረት እንዳያጋጥማቸውም ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ብድር መንግሥት ማመቻቸቱን አስታውቀዋል። ከወሰዱት ብድር ውሰጥ እስካሁን ድረስ ከ65 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆነው ተመላሽ ማድረግ መቻላቸውን ተናግረዋል። ለምርቶቻቸውም ከተለያዩ ተቋማት እና ድርጅቶች 3 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ የገበያ ትስስር በመፍጠር ተጠቃሚ መሆናቸውን አስረድተዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ተደራጅተው በዶሮ እርባታ የተሰማሩት አቶ አሰበ ተስፋዬ እንዳሉት፤ በተመቻቸላቸው የመስሪያ ቦታና ብድር በመታገዝ በመጀመሪያው ምዕራፍ 600 እንቁላል ጣይ ዶሮዎችን እያረቡ ይገኛሉ። አሁን ላይ የእንቁላል ምርቱን በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስረድተዋል። በቦኬ ወረዳ ቦኬ ጥቃ ከተማ በእንስሳት ማድለብ ከጓደኞቹ ጋር የተሰማራው ወጣት ሀብታሙ ዓለሙ በበኩሉ፤ ባገኙት 500 ሺህ ብር ብድር የመነሻ ካፒታል የጀመሩት ሥራ ውጤታማ እያደረጋቸው ይገኛል። ሰንጋዎችን በማድለብ ከአካባቢው ገበያ ባለፈ ለጭሮ እና በዴሳ ሉካንዳ ነጋዴዎች በማቅረብ ትርፋማ መሆናቸውን ነው የገለፀው።    
የቱሪዝም ዘርፍ በመደመር ዕይታ፦ ሌላው የሀገር በቀል ኢኮኖሚው ምሰሶ
Jul 24, 2026 188
ቱሪዝም በዓለም አቀፍ መድረክ ትርጉም ያለው ቦታ አለው፡፡የምሥራቅና የምዕራብ ኢኮኖሚ መመጣጠን የቱሪስቱን ብዛትና ዓይነት ጨምሯል፡፡ለቱሪዝም ያለን ሀገራዊ ዕምቅ ዐቅማችንም ከፍተኛ ነው።ይህንን በመረዳት በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም ውስጥ ከተቀመጡት አምስቱ ዓምዶች መካከል አንዱ እንዲሆን አድርገናል። ኢንዱስትሪው በሀገራችን ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊማ አካባቢያዊ ሁኔታዎች ውስጥ ትልቅ አስተዋጽዖ እንዲኖረው እንፈልጋለን፡፡የመጣውን መልካም ዕድል ወደሚጨበጥ ጥቅም ለመቀየር፣ ባለፉት ጥቂት ዓመታት፣ በፈጠራ እና በተግባራዊ ፍጥነት በርካታ መዳረሻዎችን አልምተናል፡፡ በከተማና በገጠር የሚገኙ የቱሪዝም መዳረሻዎችን አቀናጅተናል፡፡እንዲሁም ነባር የጎብኚ መዳረሻዎችን አሻሽለናል፡፡ አዳዲስ መዳረሻዎችንም አልምተናል፡፡እነዚህ ሁሉ በተለየ ትኩረት ከሠራንባቸው የለውጥ ማሳያዎቻችን መካከል ጥቂቶቹ ናቸው፡፡   ሀገራችን ከዚህ በፊት ከነበራት የጎብኚ መዳረሻዎች ላይ በእነዚህ ጥቂት ዓመታት ብዙ ጨምረናል።መዳረሻዎቹም መላው ሀገራችንን ያካለሉ ናቸው። ከሀገራችን ስፋትና ከሀብት እጥረት አንጻር ያልደረስንባቸውና በዕቅድ ላይ ያሉ ብዙ መዳረሻዎችም በቀጣይ ይገነባሉ። በእጃችን ላይ ያሉ የጎብኚ መዳረሻዎችን በአግባቡ አገልግሎት ላይ ማዋልና ከዚህም ሊገኝ የሚችለውን ሀገራዊ ጥቅም ሁሉ መሰብሰብ ተገቢና በቀጣይ ለምንጓዘው አቅጣጫ ትልቅ ግብአት የሚሆን ነው።ከዚህ አንጻርም ብዙዎቹን በፍጥነት ወደ ሥራ አስገብተናል። ትሩፋቶቹንም እያጣጣምን እንገኛለን። በእነዚህ ጥረቶች ምክንያት ሀገራችንን የሚጎበኙ የውስጥም ይሁን የውጭ ጎብኚዎች ቁጥር በጥሩ ሁኔታ እያደገ ነው። ይሁንና ዘርፉ ከፍተኛ ዕድገት እንዲያስመዘግብ ገና ብዙ መሥራት ይጠበቅብናል። ሀገራችን ከቱሪዝም ልታገኛቸው የምትችላቸውን ማኅበራዊ፣ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና አካባቢያዊ ጥቅሞች ሁሉ ከቀረው ዓለም ጋር ተወዳድራ እንድታገኝ፤ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ጎብኚ ወደ ሀገራችን መሳብ አለብን። ለዚህም የተለያዩ ስልታዊ መላዎችን (Strategies) ነድፈን እየተንቀሳቀስን እንገኛለን። የመደመር መንግሥት መፅሐፍ ከገጽ 272 - 273
በጋምቤላ ክልል የሕዝቡን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ አበረታች ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jul 23, 2026 303
ጋምቤላ ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፡- የጋምቤላ ክልልን የሕዝቡን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ አበረታች ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። የክልሉ አስፈጻሚ መሥሪያ ቤቶች የ2018 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተካሂዷል።   ርዕሰ መስተዳድሯ ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ያጋጠሙ ፈተናዎችን በመቋቋም የሕዝቡን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አበረታች ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በተለይም በማዕድን፣ በእንስሳት ሀብት ልማት እንዲሁም በሌሎች የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች የተመዘገቡት ውጤቶች ተስፋ ሰጪ ናቸው ብለዋል። ከዚሁ ጎን ለጎን በክልሉ የሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭን በማስፋት የሕዝቡን ሕይወት ለማሻሻል የተከናወኑ ሥራዎች ውጤታማ እንደነበሩ ጠቁመዋል። በቀጣይም ዘርፉን ይበልጥ በማጠናከር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት ያላሰለሰ ጥረት ይደረጋል ብለዋል። በተለይም የክልሉን የሕዝቡን ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ አበረታች ተግባራት በተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቅሰው፣ ወጪ ቆጣቢ የአሰራር ስርዓትን ተግባራዊ በማድረግ ለልማትና ለመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ተገቢው ምላሽ ይሰጣልም ብለዋል።   የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ገነት ኤሊያስ በበኩላቸው፤ ቢሮው የልማትና የመልካም አስተዳደር ዕቅዶችን በመንደፍ የሕዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሠራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ የታቀዱ ተግባራትን በየደረጃው በመገምገም የተሻለ አፈጻጸም እንዲመዘገብ የማስቻል ሥራ ሲሠራ መቆየቱንም አብራርተዋል። በዚሁ የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ ላይ የክልሉ የሴክተር መሥሪያ ቤት ኃላፊዎችና ከፍተኛ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።  
በዞኑ የሰፈነው ስላም የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን በተያዘላቸው ጊዜ አጠናቆ ወደ ስራ ለማሰገባት አስችሏል
Jul 23, 2026 316
አምቦ፤ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሸዋ ዞን የሰፈነው ስላም የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን በተያዘላቸው ጊዜ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ማድረግ እንዳስቻለ የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በምዕራብ ሸዋ ዞን ድሬ ኢንጭን ወረዳ የተገነቡ የተለያዩ መሠረተ ልማቶች የክልል ፤ ዞን እና የወረዳ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል።   የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አበበ ጨመዳ በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ በለውጡ ዓመታት የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች የሕብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ያስቻሉ ናቸው። በዞኑ የተከናወኑት የመሰረተ ልማት ግንባታዎች በህዝብ እና በመንግስት ተሳትፎ እውን ለመሆን መቻላቸውን ነው የተናገሩት።   በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም ከ 5 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡት የመሰረተ ልማቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን ገልጸዋል። የድሬ ኢንጭን ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አራርሳ ሂርጳ በበኩላቸው፤በኦሮሚያ ልማት ማህበር በወረዳው የመማሪያ ክፍሎችና ዘመናዊ ቤተመጽሐፍቶች መገንባታቸውን ገልፀዋል። በተጨማሪም የኮሪደር ልማት ፣የመንገድና የድልድይ ግንባታዎች እንደተካሔዱም ነው የተናገሩት።   በወረዳው በመንግሥት በጀትና በሕብረተሰቡ ተሳትፎ ከ278 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 23 የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን አስታውቀዋል። የክልሉ ትምህርት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ገለቱ ቱካ በበኩላቸው፤ በክልሉ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ለቅድመ መደበኛ ትምህርት በትኩረት የተሰጠ ሲሆን የትምህርት ግብአትን ለማሟላት ቅድሚያ ተሰጥቷል ነው ያሉት። ለአብነትም በዛሬው እለት ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ከተደረጉት የመሰረተ ልማቶች መካከል ለድሬ ኢንጭን ኦልማ አዳ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አስፈላጊውን ድጋፍ መድረጉን ተናግረዋል ። ምርቃቱን አስመልክቶ የድሬ ኢንጭን ወረዳ ነዋሪዎች አንዳሉት፤ በአካባቢያቸው የፀጥታ ችግር በመፈታቱ በልማት ሥራዎች ላይ በንቃት ለመሳተፍ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ነው የሚገልጹት። ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ ኡርጌሳ ቶለሳ እና ወይዘሮ ፈይነ ትሪፈሳ ፤ በአካባቢያቸው ለአገልግሎት የበቁ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች የማሕበረሰቡን የረጅም ጊዜ የልማት ጥያቄዎች የመለሱ መሆናቸውን ጠቅሰዋል ። በተለይ በአካባቢው ሰላምን ለማስፈን በመቻሉ የልማት ስራዎችን ያለምንም ስጋት ለማከናወን እንዳስቻለ አመልክተዋል።   በአሁኑ ወቅትም ለረጅም ጊዜ ሲነሱ የነበሩ የመንገድ፣ የትምህርት እና ሌሎች የልማት ስራዎች ምላሽ በማግኘታቸው ተጠቃሚ ሆነናል ብለዋል።
የኢትዮጵያ የመንገድ መሰረተ ልማቶች የሕዝብን የኢኮኖሚ ትስስር በማሳለጥ የብልፅግና ድልድይ እየገነቡ ነው
Jul 23, 2026 144
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 16/2018 (ኢዜአ) ፦የኢትዮጵያ መንገድ መሰረተ ልማቶች የሕዝብን የኢኮኖሚ ትስስር በማሳለጥ የብልፅግና ድልድይ እየገነቡ መሆኑን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ። የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር "ኢትዮጵያን የማገናኘት 75 ዓመታት፤ መንገዳችን ኃላፊነታችን" በሚል መሪ ሃሳብ 75ኛ ዓመት የአልማዝ ኢዮቤልዩን በዓል በተለያዩ መርሃ ግብሮች አክብሯል።   የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ክብረ በዓሉ ስኬቶች በመዘከር የወደፊቱን ዘመናዊ የመንገድ መሠረተ ልማት ማስፋፊያ ግቦች የሚታደሱበት አጋጣሚ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደርም ባለፉት 75 ዓመታት ትውልድ ተሻጋሪ ፕሮጀክቶችን የመፈጸም ከፍተኛ አቅም እየገነባ የመጣ ተቋም መሆኑን ጠቁመዋል። በቀጣይም ጥራታቸውን የጠበቁ፣ ዘላቂ፣ ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር የሚጣጣሙና ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ያካተቱ የመንገድ መሠረተ ልማቶችን በመገንባት ላይ ትኩረት እንደሚደረግ አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ የመንገድ መሠረተ ልማት እድገት የሕዝቡን ኢኮኖሚያዊ ትስስር በማሳለጥ የብልፅግና ድልድይ እየገነባ መሆኑንም አስረድተዋል። የሕዝቦችን ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የመሠረተ ልማት ግንባታው በይበልጥ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸው ሚኒስቴሩም ለአስተዳደሩ የሚያደርገውን ድጋፍና ክትትል አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።   የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥና የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የቦርድ ሰብሳቢ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ አስተዳደሩ በ75 ዓመታት ጉዞው የሀገሪቱ ልማት ዋነኛ ምሰሶ ሆኖ እያገለገለ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የመንገድ ሽፋን ከ180 ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ መድረሱን በመጠቆም፣ በቅርብ ዓመታት ብቻ ከ44 ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ አዳዲስ መንገዶች በመገንባት የዜጎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስተጋብር ለማሳለጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። የመንገድ መሠረተ ልማት ሕዝቦችን ከማቀራረብ ባለፈ የሀገሪቱን ኢኮኖሚያዊ እድገት እያፋጠነ ነው ያሉት ደግሞ የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መሐመድ አብዱራህማን ናቸው።   የኢትዮጵያ የመንገድ አውታር መስፋፋት ተቋማዊ የቴክኖሎጂ አቅምን ከማሳደጉም በተጨማሪ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ፋይዳ እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። በመጨረሻም ለተቋሙ ስኬት መሠረት ለጣሉ የቀድሞ አመራሮች የመንገድ ፕሮጀክቶችን እውን ለማድረግ አስተዋጽኦ ላበረከቱ መሐንዲሶች፣ ባለሙያዎችና ሠራተኞች ምስጋና አቅርበዋል።
በጋምቤላ ክልል ከ7 ሺህ 98 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ ሆኗል
Jul 23, 2026 127
ጋምቤላ፤ ሀምሌ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ7 ሺህ 98 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ መደረጉን የክልሉ ማዕድን ቢሮ አስታወቀ። ‎የጋምቤላ ክልል ማዕድን ቢሮ ኃላፊ አቶ ቻም ኡበንግ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዘርፉ በተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ ውጤቶች ተመዝግበዋል። ‎በበጀት ዓመቱ 6 ሺህ ኪሎ ግራም ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ ለማድረግ ታቅዶ ከ7 ሺህ 98 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ገቢ መደረጉን ተናግረዋል። በክልሉ በበጀት ዓመቱ ገቢ የተደረው የወርቅ ምርት ከእቅዱ በ1 ሺህ 98 ኪሎ ግራም ብልጫ ያለው ሲሆን ከቀዳሚው ዓመት ጋር ሲነፃፀር ደግሞ በ1 ሺህ 669 ኪሎ ግራም ብላጫ ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ‎ለተመዘገበው ውጤት መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት የቁጥጥር፣ የክትትልና የድጋፍ ስራዎች ተጠናክረው በመከናወናቸው መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ በበጀት ዓመቱ በተከናወነው የማዕድን ሃብት ልማት ከ6 ሺህ 890 በላይ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል የተፈጠረላቸው መሆኑንም የቢሮ ሃላፊው ገልጸዋል።
በሲዳማ ክልል አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ያደረጉ የፍራፍሬ ልማት ስራዎች እየተካሔዱ ነው
Jul 23, 2026 102
ሃዋሳ፤ ሃምሌ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ያደረጉ የፍራፍሬ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ቡና ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ልማት ባለስልጣን አስታወቀ፡፡ የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ መስፍን ቃሬ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤በክልሉ የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጥና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ፍራፍሬዎችን በማልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ተችሏል።   በክልሉ ካለው የፍራፍሬ ማሳ 43 ከመቶው በአቮካዶ ተክል የተሸፈነ ሲሆን የአፕልና አናናስ ተክልም የቤተሰብ ብልጽግና ፓኬጅ አካል ሆኖ እየተሰራበት ይገኛል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅትም በአቮካዶ ልማት የተሳተፉ ከ40 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ምርታቸውን ለይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ ዘይት አምራች ፋብሪካዎች እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለዚህም በየዓመቱ የተሻሻሉ ችግኞች በመትከል ምርታማነትን የማሳደግ ስራ እየተከናወነ ሲሆን በተያዘው ዓመትም የ4 ነጥብ 5 ሚሊዮን ችግኞች ተከላ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡ በክልሉ የጣራሜሳ አካባቢ አትክልትና ፍራፍሬ አምራችና አቅራቢ መሰረታዊ ህብረት ስራ ማህበር ሰብሳቢ አቶ ኩዬሬ ሁሬሳ፤ በአቮካዶ ልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያረጋገጥን ነው ብለዋል፡፡ በ2011 ዓ.ም 320 አርሶ አደሮችን በማቀፍ የተመሰረተው ማህበሩ፤በዋናነት ከአቮካዶ ምርት በተጨማሪ ቲማቲም፣ ጥቅል ጎመንና ሌሎች አትክልቶችን ከማምረት ባሻገር ችግኞችንም እንደሚያፈሉ ነው የተናገሩት። ማህበራቸውን ወክለው ጣሊያን ሃገር በተካሄደ አውደ ርዕይ በመሳተፍም የገበያ ትስስር ለመፍጠር እንደቻሉም ነው የሚገልጹት። በአሁኑ ወቅም በዓመት ሁለት ጊዜ የሚሰበስቡትን የአቮካዶ ምርት ለይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንደስትሪ ፓርክ እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል። ዘንድሮም ከ200 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ የአቮካዶ ምርት ለማቅረብ ማቀዳቸውን የጠቆሙት አርሶ አደሩ፤ ለተከላ የሚሆኑ ከ10 ሺህ በላይ የተሻሻሉ የአቮካዶ ችግኞችን ለአካባቢው አርሶ አደሮች ማሰራጨታቸውን ተናግረዋል፡፡      
የባሕርዳር ከተማን የተሞክሮ ማዕከል ለማድረግ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ እየተደረገ ነው
Jul 23, 2026 115
ባህርዳር፤ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፡-የባህር ዳር ከተማ የልማትና እድገት የተሞክሮ ማዕከል ለማድረግ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የአማራ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሞላ መልካሙ(ዶ/ር) ገለጹ። የባህርዳር ከተማ አስተዳደር የከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት አፈጻጸምን የሚገመግምና የአዲሱ በጀት ዓመት እቅድ ትውውቅ መድረክ ዛሬ አካሂዷል።   የቢሮ ኃላፊው ሞላ መልካሙ(ዶ/ር) እንደገለጹት በክልሉ የሚገኙ በርካታ ከተሞችን ለንግድ፣ ቱሪዝምና ለኑሮ የተመቹ ለማድረግ ሁለገብ የልማት ስራ እየተከናወነ ይገኛል። የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን በማከናወን ውብ፣ ሳቢና ማራኪ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የባህር ዳር ከተማ በሰፋፊ የአስፋልት መንገዶች፣ በኮሪደር ልማት፣ በስማርት ሲቲ ትግበራ፣ የአረንጓዴ ልማትና ሌሎች የልማት ስራዎች ካሳየችው እድገት በመነሳት የተሞክሮ ማእከል ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። እየተካሄደ የሚገኘው ሁሉን አቀፍ ልማት ከተማዋን ለኢንዱስትሪ፣ ኮንፈረንስ ቱሪዝም፣ ንግድና ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ምቹ ሁኔታ የፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል። ቢሮው በከተማዋ የሚካሄዱ የልማት ስራዎች በጥራትና በፍጥነት እንዲከናወኑ እያደረገ ያለውን ክትትልና ድጋፍ አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።   የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ አቶ አስሜ ብርሌ በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በከተማዋ እየተገነቡ ያሉ የልማት ስራዎች ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ የሰጡ ናቸው ብለዋል። የተገኙ ስኬቶችን አጠናክሮ በማስቀጠል በቀጣይ የዲጂታል መሠረተ ልማትን የበለጠ በማስፋፋት የአገልግሎት አሰጣጥ ችግርን ለመቅረፍ በተሻለ መንገድ እንደሚሰራ አስገንዝበዋል። በበጀት ዓመቱ የተመዘገቡ ስኬቶች የሁሉም ባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ሥራ ውጤት ናቸው ያሉት ደግሞ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የከተማ አስተዳደሩ ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ስራ አስኪያጅ አቶ ተሻገር አዳሙ ናቸው። በመጀመሪያውና 2ኛው ዙር ብቻ ስምንት ነጥብ ስድስት ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ማጠናቀቅ መቻሉን ጠቁመው 3ኛው ዙርም በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ አረጋግጠዋል። የተቀናጀ የኮሪደር ልማት ሥራዎችን በማፋጠን የባሕርዳር ከተማን ሁለንተናዊ ተመራጭነት በተጨባጭ የማረጋገጥ ጉዳይ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል። በ2019 በጀት ዓመት የታቀዱ የልማት ሥራዎችን በጥራትና በፍጥነት በማከናወን የከተማዋን ህዝብ ተጠቃሚ ለማደረግ በቅንጅት እንደሚሰራ አስገንዝበዋል። በመድረኩ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች፣ ባለሙያዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላተ ተሳትፈዋል።
በአሪ ዞን የመኸር አዝመራን ስኬታማ ለማድረግ የግብአት አቅርቦትና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ላይ እየተሰራ ነው
Jul 23, 2026 228
ጂንካ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ በአሪ ዞን የመኸር አዝመራን ስኬታማ ለማድረግ የግብአት አቅርቦትና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ላይ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ ። በዞኑ የ2018/19 የመኸር አዝመራ የማስጀመሪያ መርሃ- ግብር እየተካሄደ ነው።   የአሪ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ገረመው ኃይለማርያም በዚሁ ወቅት እንዳሉት የግብርና ዘርፉን በማዘመን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የስራ እድል ፈጠራን ለማስፋት እየተሰራ ነው ። በዞኑ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ የተሻለ የግብአት አቅርቦት እንዲኖር ከማድረግ ባለፈ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማጎልበት ሞዴል አርሶ አደሮችን ለማፍራት እየተቻለ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ በበጋው ወራት የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የመኸር አዝመራውን ውጤታማ ለማድረግ መደላድል ፈጥረዋል ነው ያሉት። የአሪ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ጉራልቅ ይዥማልቅ በበኩላቸው፤ በዞኑ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖን የሚቋቋም ግብርናን እውን በማድረግ ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል።   ለዚህም የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃን ጨምሮ የአረንጓዴ ልማት ስራዎች በተለየ ትኩረት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ግብርናን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ በመስኖ ልማት ላይ ትኩረት ለማድረግም የገፀ ምድርና የከርሰ ምድር የውሃ አማራጮች ጥቅም ላይ መዋላቸውን አስረድተዋል። የመኸር አዝመራውን በታቀደው ልክ ስኬታማ ለማድረግም አርሶ አደሮች የግብርና ባለሙያዎችን ምክር በመቀበል፣ የተሻሻሉ ዝርያና ቴክኖሎጂዎችን እንዲጠቀሙ እየተደረገ ነው ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ ከጂንካ ዩኒቨርስቲ ፣ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ፣ከጂንካ ግብርና ምርምር ማዕከል እና የአጋር ድርጅት ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የኢትዮ-ቴሌኮም ቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የመሪነት ሚና መወጣት የሚያስችል ነው 
Jul 23, 2026 364
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮ-ቴሌኮም ቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የመሪነት ሚና መወጣት የሚያስችል መሆኑን የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ገለጹ። የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ የተቋሙን የ2018 በጀት ዓመት እና የቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ አፈፃፀም አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ በሰጡት መግለጫ፣ ኢትዮ ቴሌኮም ባለፉት ሰባት ዓመታት ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በትጋት ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮም በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት 215 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ገቢ በማግኘት የእቅዱን 99 ነጥብ 7 በመቶ ማሳካቱንም ገልጸዋል። ይህ ገቢ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ33 ነጥብ 2 በመቶ እድገት ያሳየ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት የቴሌብር ተጠቃሚዎች ቁጥር 60 ነጥብ 5 ሚሊዮን መድረሱን አስታውቀዋል ። ባለፈው ዓመት የተጀመረውና ለሶስት ዓመታት የሚተገበረው የቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ ሁለንተናዊ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገትን ለማፋጠን ያለመ መሆኑን አስገንዝበዋል። ስትራቴጂው ተቋሙ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የድርሻውን እንዲወጣ የሚያስችልና ለአፍሪካ አጀንዳ 2063 ብሎም ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 መሳካት ጠንካራ መሰረት የሚጥል መሆኑንም ተናግረዋል። በስትራቴጂው የአንድ ዓመት አፈፃፀም በርካታ የኔትወርክ ተደራሽነት እና የማዘመን ስራዎች መከናወናቸውን አብራርተዋል። በዚህም 603 አዳዲስ የሞባይል ጣቢያዎች ተገንብተው ወደ ስራ መግባታቸውን ገልጸው፣ ይህም አጠቃላይ የሞባይል ጣቢያዎችን ቁጥር 10 ሺህ 613 ማድረሱን ተናግረዋል። በ195 የገጠር ሞባይል ጣቢያዎች መገንባታቸውንም በዚህም 117 ወረዳዎች ተደራሽ መሆናቸውን ገልፀዋል። ይህም ተደራሽነትን ማስፋትና አካታችነትን ማረጋገጥ ማስቻሉን ነው ዋና ስራ አስፈፃሚዋ የገለፁት። በ195 የገጠር ሞባይል ጣቢያዎች በመገንባታቸው 117 ወረዳዎች ላይ የኔትወርክ ተደራሽነትን በማስፋት አካታችነትን ማረጋገጥ ያስቻለ ትልቅ ስኬት መሆኑን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ 264 ከተሞች የአራተኛው ትውልድ (4ጂ) ኔትወርክ አገልግሎት ማግኘት መቻላቸውን ተናግረዋል። ሰባት ተጨማሪ ከተሞች የ5ጂ አገልግሎት ማግኘታቸውን ተከትሎም፣ የ5ጂ ተጠቃሚ ከተሞች ቁጥርም 33 መድረሱን አስታውቀዋል። በአጠቃላይ ሁለንተናዊ የቴክኖሎጂ እና የመሠረተ ልማት ማስፋፊያ ስራዎችን መሠረት በማድረግ፣ የኢትዮ ቴሌኮም አጠቃላይ የደንበኞች ቁጥር 90 ነጥብ 1 ሚሊዮን መድረሱን ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ ገልጸዋል።
በጅማ ዞን ከ1 ሺህ 600 በላይ አርሶ አደሮች ወደ ኢንቨስትመንት ተሸጋግረዋል
Jul 23, 2026 116
ጅማ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ በ2018 በጀት ዓመት በጅማ ዞን ከ1 ሺህ 600 በላይ አርሶ አደሮች ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን የዞኑ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ወይዘሮ ዘሊካ ቡላ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በዞኑ ለኢንቨስትመንት ያለውን አቅም ወደ ልማት ለመቀየር የአሠራርና የሕግ ማዕቀፎች ተዘርግተዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ በግብርና፣ አነስተኛና ጥቃቅን ኢንተርፕራይዞችና በኅብረት ሥራ ማኅበራት ተሰማርተው የነበሩ 1 ሺህ 739 አልሚዎች ሀብት አፍርተው ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ገልጸዋል። ባለሀብቶቹ ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩት 5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ካፒታል በማስመዝገብ መሆኑን ጠቁመዋል። አልሚዎቹ በተሰማሩበት ዘርፍ ውጤታማ ሆነው ወደ ኢንቨስትመንት እንዲሸጋገሩ በመንግሥት 8 ሺህ 27 ሄክታር መሬት የቀረበ ሲሆን፣ 120 ሚሊዮን ብር ብድር መሰጠቱን ገልጸዋል። ፕሮጀክቶቹ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገቡም ከ22 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች በቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ይፈጥራሉ ብለዋል። በዞኑ 2 ሺህ 495 የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች በሥራ ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው እነዚህ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ከ55 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች በቋሚነትና በጊዜያዊነት የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ተናግረዋል። በዞኑ በዴዶ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ጃፈር አብዱልቃድር፤ በ2012 ዓ.ም ተደራጅተው በ50 ሺህ ብር መነሻ ካፒታል በግብርና ሥራ ላይ ተሰማርተው እየሠሩ እንደነበር ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ካፒታላቸውን በማሳደግና ትርፋማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ገልጸዋል። ማኅበራቸው ከ60 በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ጠቅሰው፣ በቀጣይም ሥራውን በማስፋት በርካታ ወጣቶችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ አቅደው እየሠሩ እንደሚገኙ አንሥተዋል። ወጣት ሚሊዮን ዳመነ በበኩሉ፤ በመንግሥት በተመቻቸላቸው የብድር አገልግሎት በሕንፃ ግንባታ ዘርፍ በማኅበር ተደራጅተው በመሥራት ካፒታላቸውን በማሳደግ ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገር መቻላቸውን ተናግሯል። በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ዞኑ ምቹ እና በርካታ አማራጮች ያለው ከመሆኑም ባሻገር መንግሥት የሚያደርግላቸው ድጋፍ እና ክትትል የበለጠ ለመሥራት ተነሣሽነትን እንደፈጠረላቸው አስታውቋል። በዞኑ በቀጣይ የኢንቨስትመንት ቅበላ አቅምን ለማሳደግ እየተሠራ መሆኑም ተጠቅሷል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም