ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ለሀገር ታማኝ ሆኖ መስራትና ልማትን መደገፍ የሚያኮራ ተግባር ነው- ተሸላሚ ግብር ከፋዮች
Sep 1, 2026 143
አሶሳ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፡- ለሀገር ታማኝ ሆኖ መስራትና ልማትን መደገፍ የሚያኮራ ተግባር መሆኑን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ተሸላሚ የሆኑ ግብር ከፋዮች ገለጹ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ገቢዎች ባለስልጣን ለታማኝ ግብር ከፋዮች የእውቅና ሽልማትና የምስጋና መርሃ ግብር አካሂዷል።   ከታማኝ ግብር ከፋዮች መካከል አቶ ሙፍቲ ሀሊፋ፤ ግብርን በታማኝነት መክፈል ለሀገር ልማትና ለዜጎች አገልግሎት ታማኝ ሆኖ መገኘት መሆኑን ገልጸዋል። በወርቅ ማእድን ስራ ላይ የተሰማሩትና በበጀት ዓመቱ ከ37 ሚሊየን ብር በላይ ገቢ የከፈሉት አቶ ሙፍቲ፤ የክልሉን ልማት ለማፋጠንና ለዜጎች ተጠቃሚነት በመስራታቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል።   ሌሎችም በታማኝነት ግብር ሲከፍሉ ለራሳቸው፣ ለህዝባቸውና ለሀገራቸው ታማኝ መሆናቸውን እያስመሰከሩ መሆኑን አንስተው በዚሁ መቀጠል አለብን ብለዋል። ሌላኛው ታማኝ ግብር ከፋይና ተሸላሚ አቶ እዮብ ዲታሞ፤ ግብይትን በደረሰኝ ብቻ መፈጸም ወጪና ገቢን በቀላሉ ከመለየት በተጨማሪ ግብራቸውን በመረጃ ለመክፈል እንዳገዛቸው ገልጸዋል።   ድርጅታቸው ለተከታታይ ዓመታት ታማኝ ግብር ከፋይ በመሆን እውቅና እና ሽልማት ማግኘቱን አስታውሰው፤ በቀጣይም በታማኝነታችን ለሀገራችን የምናደርገውን ሁለንተናዊ አስተዋጽኦ አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ሌላኛው ተሸላሚ የሆኑት አቶ መብራቱ የኋላ፤ የግብር መክፈል ጉዳይ ለሀገር እና ለዜጎች ተጠቃሚነት በመሆኑ ሁላችንም የዜግነት ግደታችንን ልንወጣ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።   ለሀገር ታማኝ ሆኖ መስራትና ልማትን መደገፍ የሚያኮራ ተግባር መሆኑን ያነሱት ግብር ከፋዮቹ በዚሁ ተግባራቸው የሚቀጥሉ መሆኑን አረጋግጠዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የታደሙ ታማኝ ግብር ከፋዮች ከምስጋና ጭምር የሚዳሊያ እና የዋንጫ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።  
በዲላ ከተማ የተከናወኑ ልማቶች የሕዝብን የልማት ጥያቄዎች እየመለሱ መጥተዋል - የከተማው ምክር ቤት አባላት
Sep 1, 2026 81
ዲላ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፡-በዲላ ከተማ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የሕዝብን ጥያቄዎች እየመለሱ በመምጣታቸው ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው የከተማው አስተዳደር ምክር ቤት አባላት ገለጹ። አባላቱ በዲላ ከተማ የተከናወኑና በሂደት ላይ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶችን ዛሬ ተዘዋውረው ተመልክተዋል። በአባላቱ ምልከታ ከተደረገባቸው የልማት ስራዎች መካከል ለተጠቃሚዎች የተላለፉ የጋራ መኖሪያ ቤቶች፣ የአስፋልት መንገድ ግንባታ፣ የኮሪደር ልማት፣ የህዝብ መዝናኛ ፓርክ፣ የዲላ መሶብ አንድ ማዕከል የአገልገሎት መስጫ ይገኙበታል።   የልማት ፕሮጀክቶቹ በምክር ቤት ከአባላት በተደጋጋሚ ለሚነሱ የህዝብ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ መሆናቸውንም አባላቱ ተናግረዋል። ከምክር ቤቱ አባላት መካከል ወይዘሮ አበራሽ ወራሳ ለኢዜአ እንደገለጹት ከተማ አስተዳደሩ ለህብረተሰቡ የልማት ጥያቄ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ለአገልግሎት የበቁ ፕሮጀክቶች አመላካች ናቸው። በተለይ የአስፓልት መንገድን ጨምሮ የመሰረተ ልማት ዝርጋታ እንዲሁም የኮሪደር ልማትና የመኖሪያ ቤት አቅርቦት የሚበረታቱና በቀጣይም ተጠናክረው መቀጠል ያለባቸው ናቸው ብለዋል። "ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዲላ ከተማ እየታየ ያለው ፈጣን የልማት ጉዞ ተስፋ የሚሰጥ ነው" ያሉት ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ መሐመድ ጉሚ ናቸው። የልማት ሥራዎቹ የከተማዋን ነዋሪ የልማት ጥያቄዎች ከመመለስና የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር አንጻር ጉልህ አስተዋጾ እያደረጉ በመሆኑ ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ብለዋል። በከተማው የህዝብን የልማት ጥያቄ ለመመለስ በሚከናወኑ ተግባራት እንደ ምክር ቤት አባልነታቸው ህዝብን በማስተባበርና አስፈላጊውን ክትትልና ድጋፍ በማድረግ አስተዋጾ ማድርጋቸውንም ጠቁመዋል። ወይዘሮ መሠረት በየነ የተባሉ ሌላው አባል በበኩላቸው፣ በከተማው የተከናወኑ የልማት ስራዎች የከተማዋን ገጽታና ደረጃ እየቀየሩ መምጣታቸውን ነው የገለጹት። ልማቱ የበርካቶችን ሕይወት ያቀናና የሥራ ዕድል የፈጠረ በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል። የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ መስፍን ደምሴ (ዶ/ር) አስተዳደሩ ህብረተሰቡን በማስተባበር ከነዋሪው ለሚነሱ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ምላሽ እየሰጠ መሆኑ ተናግረዋል። ፈጣንና ዘመናዊ አገልግሎት ለመስጠት መሶብ የአንድ ማዕከል አገልገሎትን ጨምሮ የዲጀታል አሰራርን በተለያዩ ሴክተር ተቋማት ተግባራዊ ማድረጉንም አመልክተዋል። ይህም የከተማዋን እድገት ከማፋጠን ባለፈ ለነዋሪዎቿ የተሻለ የኑሮ አካባቢን ለመፍጠር ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን አስረድተዋል።  
በሸገር ከተማ አርሶ አደሩን ወደ ኢንቨስተርነት የማሸጋገር ስራ ውጤት እያመጣ ነው
Sep 1, 2026 90
ሸገር ፤ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፡- በሸገር ከተማ አርሶ አደሩን ከባህላዊ የአሰራር ዘይቤ በማላቀቅ ወደ ኢንቨስተርነት የማሸጋገር ስራ ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገቡን የኦሮሚያ ክልል ከተማ ልማትና ቤቶች ቢሮ ኃላፊ አቶ መሀመድ ጉዬ ገለጹ። የሸገር ከተማ የገበሬዎች ቀን «ዘመናዊ ገበሬና ዘመናዊ ግብርና ለአጠቃላይ ብልፅግና» በሚል መሪ ቃል በከተማው ሱሉልታ ክፍለ ከተማ በተለያዩ ሥነ-ሥርዓቶች እየተከበረ ይገኛል። አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግም የባዛር እና ኤግዚቢሽን መርሃ ግብር የተዘጋጀ ሲሆን፣ የግብርና ምርቶች፣ የግብርና ማሽነሪዎችና ግብዓቶች ለእይታ ቀርበዋል።   በመርሃ ግብሩ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል ከተማ ልማትና ቤቶች ቢሮ ኃላፊ አቶ መሀመድ ጉዬ፤ ሸገር በጥቂት ዓመታት ቆይታ ውስጥ ታላላቅ ስኬቶችን እያስመዘገበች መሆኗን ገልጸዋል። የሸገር ከተማ ከተመሰረተች በኋላ በተለይም በከተማ ግብርና የተሰማሩ አርሶ አደሮችን የግብርና ቴክኖሎጂዎች፣ የግብዓት አቅርቦት፣ ሙያዊ ድጋፍና መሰል ጉዳዮችን በማቅረብ ውጤታማ እንዲሆኑ በተሰራው ስራ ውጤት እየተገኘ እንዳለ አመልክተዋል። በመሆኑም በከተማ አስተዳደሩ አርሶ አደሩን ከባህላዊ የአሰራር ዘይቤ በማላቀቅ ወደ ኢንቨስተርነት የማሸጋገር ስራ ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገቡን ተናግረዋል። የሸገር ከተማ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ(ዶ/ር) በበኩላቸው በመደመር እሳቤ ባለፉት ዓመታት ከተማዋን የኢኮኖሚ፣ የኢንቨስትመንትና የኢንዱስትሪ ማዕከል ለማድረግ ከተከናወኑት ተግባራት ጎን ለጎን የአርሶ አደሩንና የከተማዋን ሕዝብ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተሰራው ሥራ በርካታ ውጤቶች ተገኝተዋል ብለዋል። ከተማው የአርሶ አደሩን የኢኮኖሚ አቅም በመገንባትና በማሳደግ በጋራ የምታድግ ከተማ መሆኗንም ገልጸዋል።   የእርሻ ሜካናይዜሽንና ቴክኖሎጂን በማስፋት፣ የግብርና ግብአቶችን በወቅቱ በማቅረብ እንዲሁም የአርሶ አደሩን የሥራ ባህል በመለወጥ በርካታ አርሶ አደሮችን ወደ ኢንቨስትመንት ማሸጋገር መቻሉንም ለአብነት አንስተዋል። እንዲሁም የንግድ ቦታዎችንና የተለያዩ ሁኔታዎችን በማመቻቸትና የገበያ ትስስር በመፍጠር ረገድ በርከታ ስራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል። በከተማው በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የግብርና ክላስተር አስተባባሪ አቶ ግርማ ሀይሉ እንደገለጹት፤ አስተዳደሩ ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከር ቀደም ሲል ከመሬቱ ይፈናቀል የነበረው አርሶ አደር አሁን በመሬቱ ላይ ባለቤት ሆኖ በተለያዩ ዘርፎች በመደራጀት ምርትና ምርታማነቱን እያሳደገ ይገኛል።   በመደመር መንግስት ባለፉት ዓመታት የተሰሩ ሥራዎች የፖለቲካ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ስብራቶችን መታደግ መቻሉንም አንስተዋል። በዚህም አርሶ አደሩንና ግብርናውን በማዘመን የከተማዋን የዕድገት ጉዞ ለማሳደግና አጠቃላይ ብልጽግናን ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን የዛሬው መርሃግብር ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የቻይና ባለሀብቶች እሴት በተጨመረበት የቡና ምርት ላይ እንዲሳተፉ ትፈልጋለች - የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን
Sep 1, 2026 167
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ) ፦ የኢትዮጵያን ከፍተኛ የኢንቨስትመንት አቅም በመጠቀም፣ የቻይና ባለሃብቶች እሴት የሚጨምሩ የቡና ኢንዱስትሪዎችን በሀገሪቱ ውስጥ እንዲገነቡ ፍላጎት መኖሩን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ዝናቡ ይርጋ ገለጹ። “2026 የዩናን-ኢትዮጵያ የሁለትዮሽ ንግድና የቡና ኢኮኖሚ ትብብር ማስተዋወቂያ ጉባኤ” በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ዝናቡ ይርጋ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የቻይና ባለሀብቶች በኢትዮጵያ እሴት የተጨመረበት የቡና ምርት ላይ እንዲሳተፉ ፍላጎት አላት። ለዚህም ኢትዮጵያ ትልቅ የኢንቨስትመንት አቅም እንዳላት ጠቅሰው የቻይና ባለሀብቶች በኢትዮጵያ እሴት የሚጨምሩ የቡና ኢንዱስትሪዎችን እንዲገነቡ ፍላጎት መኖሩን አብራርተዋል። የቻይና ባለሀብቶች በቡና ምርት፣ በዘመናዊ ማቀነባበሪያ፣ ከምርት ጀምሮ ለገበያ እስከሚቀርብ ባለው ሂደት የዲጂታል ክትትል መስኮች ኢንቨስት ማድረግ የሚችሉበት ሰፊ ዕድል መኖሩን ተናግረዋል። የአየር ንብረት ለውጡን የሚቋቋም የግብርና ሥርዓት መኖሩ ሌላው ምቹ ሁኔታ መሆኑን አንስተው፤ በዘመናዊ ማሸጊያ ኢንቨስት ማድረግ የሚችሉበት ምቹ ሁኔታ መኖሩንም አብራርተዋል። የቻይናዋ ዩናን ግዛት የንግድ መምሪያ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሊ ዪ በበኩላቸው፤ በዩናንና ኢትዮጵያ መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ በእጥፍ እያደገ መምጣቱን አሳውቀዋል። የዩናን ግዛት በዚህ የንግድ ማስተዋወቂያ መድረክ ላይ 20 የቡና ኩባንያዎችን ይዞ መምጣቱን ጠቅሰው፤ ትኩረታቸውም ከኢትዮጵያ ጥራት ያለው አረንጓዴ ቡና ግዥና ንግድን ማስፋት መሆኑን ገልጸዋል። ዩናን በቻይና የቡና ኢንዱስትሪ ዋና ማዕከል እንደሆነች ጠቅሰው፣ ትላልቅ ቡና ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ የተስፋፉባት መሆኑን አመልክተዋል። ይህም ከኢትዮጵያ የሚገኘውን ጥራት ያለው ጥሬ ቡና በዩናን በማቀነባበር እሴት ጨምሮ ወደ ቻይናና ዓለም ገበያ ለማቅረብ ዕድል የሚፈጥር መሆኑን አስረድተዋል። የቻይና ኤምባሲ የኢኮኖሚና ንግድ ካውንስለር ሊዩ ሺያኦጓንግ በበኩላቸው፤ ቻይና የኢትዮጵያ ትልቋ የንግድ አጋርና የኢንቨስትመንት ምንጭ መሆኗን ገልጸዋል። ቻይና ለኢትዮጵያ ምርቶች የዜሮ ታሪፍ የገበያ ዕድልን ጨምሮ የንግድ ማመቻቸት ሥርዓቶችን በማስፋት የኢትዮጵያ ምርቶች በቻይና ገበያ ተደራሽ እንዲሆኑ እየሠራች መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይም የዩናን ግዛት እና ኢትዮጵያ በአየር ንብረትና በጂኦግራፊ ተመሳሳይ ባህሪያት ያላቸው መሆኑን አመልክተው፤ በቡና ዘርፍ የጋራ ትብብር ለማስፋት የተሻለ መሠረት መፍጠሩን ገልጸዋል። የቻይና ገበያ በተለይም ለከፍተኛ ጥራት ያለው የቡና ጥሬ ዕቃ ፍላጎቱ እየጨመረ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከኢትዮጵያ የሚገኘውን ልዩ ጣዕምና ጥራት ያለው ቡና ወደ ዩናን በማስገባት በማቀነባበርና በማስተዋወቅ የገበያ እሴቱን ለማሳደግ ፍላጎት መኖሩን አስረድተዋል። እንደ ካውንስለሩ ገለጻ፣ ይህ ትብብር በቡና ንግድ ብቻ የሚወሰን ሳይሆን የኢንቨስትመንት፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የኢንዱስትሪ ልማት ዕድሎችንም የሚያሰፋ ነው። በመድረኩ የኢትዮጵያና የዩናን የንግድና ኢንቨስትመንት ተወካዮች የቡና ንግድን፣ የገበያ ትስስርንና የጋራ የኢንቨስትመንት ዕድሎችን በማስፋት ዙሪያ ውይይት አድርገዋል።
ከውስጣዊ ዐቅም ትንሣኤ እስከ ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት፡ የኢትዮጵያ የጽናት ምዕራፍ!
Sep 1, 2026 95
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፋዊ ኢኮኖሚያዊ ቀውሶችን እና ጂኦ-ፖለቲካዊ ጫናዎችን በጽናት በመመከት፣ ፈተናን ወደ ታሪካዊ ዕድል መቀየር የሚቻለው በውስጣዊ ዐቅም ልዕልና እንጂ በውጭ ጥገኝነት እንዳልሆነ በተግባር አሳይታለች። መንግሥት ባለፉት የለውጥ ዓመታት የነደፋቸው የልማት እና የሪፎርም ማዕቀፎች ሀገሪቱን ከውጭ ተጽዕኖዎች በሂደት በማላቀቅ፣ በማንኛውም ፈተና ውስጥ የማይበገር ሁሉን አቀፍ ሉዓላዊነት እንዲገነባ መሠረት እየጣለ ይገኛል።   በግብርናው ዘርፍ የተደረገው ሪፎርም ምርታማነትን እና የዝናብ ጥገኝነትን በማሻሻል የኢትዮጵያን የረጅም ዘመን የተረጂነት ታሪክ በመስበር የምግብ ሉዓላዊነትን ወደሚያረጋግጥ ዐዲስ ምዕራፍ ተሸጋግሯል። በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት፣ በክላስተር ግብርና እና በቴክኖሎጂ አጠቃቀም የተመዘገበው እመርታ ከውጭ በሚገባ የስንዴ ዕርዳታ ላይ የተመረኮዘውን የሀገራችንን እውነታ ቀይሮ፣ በሀገር ውስጥ ምርት ራስን ከመቻል አልፎ ለጎረቤት ሀገራት የተረፈ ምርትን ማቅረብ ያስቻለ ተጨባጭ ውጤት አሳይቷል።   የአምራች ኢንዱስትሪ የማምረት ዐቅምን እና ዓለማቀፍ ተወዳዳሪነትን በማሻሻል፣ የማዕድን ምርት ጥራት እና እሴትን በመጨመር፣ የውጭ ዕዳ ጫናን በመቀነስ እና የተረጋጋ የውጭ ምንዛሪ ገበያ በመፈጠር የተረጋጋ ማክሮ ኢኮኖሚን በማረጋገጥ፣ የዋጋ ግሽበትን በመቆጣጠር እመርታዊ ስኬቶች ተመዝግበዋል። እንደ ለሚ ኩራ እና ቂሊንጦ ያሉ የኢንዱስትሪ ፓርኮች የቴክኖሎጂ ሽግግርን እያረጋገጡ ይገኛሉ። የሲሚንቶ፣ የብረታብረት እና የኬሚካል ምርቶች የሀገር ውስጥ ፍላጎት በብቃት እንዲሸፈን ተደርጓል።   ከዚህም በተጨማሪ እንደ ወርቅ እና ታንታለም ያሉ ወሳኝ ማዕድናትን ከጥሬ ዕቃ ንግድ አሠራር ወጥተው በሀገር ውስጥ እንዲጣሩ እና እሴት ተጨምሮባቸው ወደ ውጭ እንዲላኩ የተደረገው ጥረት የኢኮኖሚ ጽናታችንን አጠናክሯል። የውጭ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርቶች የመተካት ፖሊሲ እና የታክስ ማሻሻያዎች ሀገራዊ ዐቅምን እያጎለበቱ፣ የበጀት ነፃነታችንን እያረጋገጡ ቀጥለዋል። በዲጂታል፣ በኢነርጂ፣ በሰው ሀብት ልማት እና በጤና መስኮች የተሠሩ ሰፋፊ ማሻሻያዎች በቴክኖሎጂ፣ በኃይል እና በሕክምና ግብዓት አቅርቦት ራስን የምትችልበትን ዐቅም ፈጥረዋል። እንደ "ፋይዳ" ብሔራዊ መታወቂያ ሥርዐት እና የዲጂታል ክፍያ ሥርዐት የዜጎችን ዳታ ከውጭ ተቋማት ሞግዚትነት ነፃ አውጥተዋል። የቂሊንጦ ፋርማሲዩቲካል ፓርክ እና ሌሎች የሀገር ውስጥ መድኃኒት ማምረቻ ኢንዱስትሪዎች መሠረታዊ መድኃኒቶችን፣ የሕክምና ኦክስጅን እና የክትባት አቅርቦቶችን በሀገር ውስጥ በማምረት ከውጭ ይገባ የነበረዉን በማስቀረት በጤና ዘርፍሉ አስቻይ የሉዓለዊነት ዐቅም ፈጥረዋል። ከዚህ ባለፈም የወጣቶችን ፈጠራ ሥነ-ምኅዳር እና የዲጂታል ክሕሎት ማሳደግ የሚያስችሉ የስታርት-አፕ ሥራዎች የውስጣዊ ዐቅማችን ማዕቀፍ አካል ሆነዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን ጨምሮ የታዳሽ ኃይል ማመንጫዎች እና የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር የኃይል አቅርቦት ዐቅማን በማሳደግ ቀጣናዊ የታዳሽ ኃይል ምንጭ ማድረግ አስቸለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነትን በመቋቋም ተምሳሌት መሆን ተችሏል። በዲፕሎማሲ እና በጂኦ-ፖለቲካ ዓውድም ሀገሪቱ በብሪክስ (BRICS) አባልነት፣ በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና (AfCFTA) እና በሌሎች ዓለም አቀፍ መድረኮች የጋራ ተጠቃሚነትን እና ነጻ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲን በማስቀደም የሉዓላዊነት ዐቋሟን አጠናክራለች። የኢትዮጵያ የፀጥታ ተቋማትና የመከላከያ ሠራዊት የገነባው የላቀ ወታደራዊ ዐቅም እና በራስ የማምረት ውስጣዊ ዐቅምም የመቻላችን ምስክር ከመሆን ባለፈ የሀገራዊ ክብር መገለጫ ሆኗል። የእነዚህ ስኬቶች እውነተኛ ባለቤት የሆነው ሕዝባችን ዛሬ ላይ በመደመር መንግሥት መሪነት የዘመናት የተረጂነት አስተሳሰብን ሰብሮ በመውጣት በሁሉም መስክ ዐዲስ ታሪክ መጻፍ ጀምሯል።
ለአዲስ ዓመት በዓል የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይኖርና ሕገ ወጥ ግብይትን ለመቆጣጠር ቅድመ ዝግጅት ተጠናቋል
Sep 1, 2026 90
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በመጪው የአዲስ ዓመት በዓል የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይከሰትና ሕገ ወጥ ግብይትን ለመቆጣጠር አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ስራ መጠናቀቁን የአዲስ አበባ ከተማ ንግድ ቢሮ ኃላፊ ሀቢባ ሲራጅ አስታወቁ። የቢሮ ኃላፊዋ ሀቢባ ሲራጅ የ2019 ዓ.ም አዲስ ዓመት በዓልን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ፣ ለአዲስ ዓመት በዓል ግብይት መሳለጥ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት ተጠናቋል። የበዓሉ ወቅት ከፍተኛ የገበያ ፍላጎትን መነሻ በማድረግ ሊከሰቱ የሚችሉ የዋጋ ጭማሪ፣ የምርት እጥረትና ሕገ ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም የበዓል ገበያን ለማረጋጋት 7 የሰብል፣ የአትክልትና ፍራፍሬ፣ የፋብሪካ ምርቶች መሸጫ፣ 5 የእንስሳት ቄራ ማዕከላትና 264 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ሳምንቱን ሙሉ አገልግሎት እንደሚሰጡ አስታውቀዋል። በአዲስ አበባ ንግድ ሥራዎች ኮርፖሬሽንና በኅብረት ሥራ ማኅበራት ትብብር ጤፍ፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ የእርድ እንስሳት፣ ዶሮዎችና እንቁላል፣ የምግብ ዘይትና ሌሎች አስፈላጊ ምርቶች በስፋት ለገበያ እንደሚቀርቡ አስረድተዋል። በበዓሉ ወቅት ሰው ሠራሽ የምርት እጥረት በሚፈጥሩና ዋጋ በሚጨምሩ ሕገ ወጥ ነጋዴዎች ላይ ቁጥጥር በማድረግ አስፈላጊውን አስተዳደራዊና ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድ አሳስበዋል። የመጋዘን ፍተሻ፣ የመለኪያ መሣሪያዎች ትክክለኛነት፣ የአገልግሎት ጊዜያቸው ያለፈባቸው ምርቶችን የማረጋገጥና የመቆጣጠር ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አብራርተዋል። ኅብረተሰቡም በዓሉን ምክንያት በማድረግ በግብይት ሥርዓቱ ላይ አሻጥር በመሥራት የሕግ ጥሰትና ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉ አካላትን ሲመለከት በነጻ ስልክ ቁጥር 8588 ጥቆማ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርበዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን ቡሳ ጎኖፋን ለማጠናከር በበልግ ወቅት የለማው ምርት ተሰብስቧል
Sep 1, 2026 82
ነገሌ ቦረና ፤ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፡-በምስራቅ ቦረና ዞን ቡሳ ጎኖፋን ለማጠናከር በዘንድሮ በልግ አዝመራ ከለማው መሬት ከሰባት ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የዞኑ ቡሳ ጎኖፋ ጽህፈት ቤት ገለጸ። ቡሳ ጎኖፋ በኦሮሚያ ክልል በተለያየ ምክንያት ለችግር ለሚጋለጡ ወገኖች ፈጣንና ዘላቂ ድጋፍ ለመስጠት፣ የአደጋ ስጋትን ለመቀነስ እንዲሁም ህብረተሰቡ እርስ በእርስ የሚረዳዳበትን ባህላዊና ማህበራዊ እሴቶች ማዕከል በማድረግ የተዋቀረ ተቋም ነው። በተለይም በክልሉ ድርቅና የተፈጥሮ አደጋዎች በተደጋጋሚ በሚከሰቱባቸው እንደ ምስራቅ ቦረና ባሉ አካባቢዎች ተቋሙ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና አደጋዎችን በራስ አቅም ለመከላከል በትኩረት እየሰራ ይገኛል። በዞኑ በበልግ አዝመራ ከለማው መሬት የተሰበሰበው ከሰባት ሺህ ኩንታል በላይ ምርትም የቡሳ ጎኖፋን የምግብ እህል ክምችት ከማጠናከሩ ባሻገር፣ ድንገተኛ አደጋዎች ሲከሰቱ በራስ አቅም ፈጣን ምላሽ ለመስጠት አስተዋጽኦ ይኖረዋል። የምስራቅ ቦረና ዞን ቡሳ ጎኖፋ ጽህፈት ቤት ተወካይ አቶ ዋሪዎ ሀሰን ለኢዜአ እንዳስታወቁት ጽህፈት ቤቱ በዞኑ ለሚከሰቱ ሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት በተለያዩ አካባቢዎች ሰብሎችን የማምረት እንቅስቃሴ ውሰጥ ገብቷል። በዚህ ረገድ ለመጀመሪያ ጊዜ በዞኑ በዘንድሮ የበልግ አዝመራ በ172 ሄክታር መሬት ላይ ካለማው ስንዴ፣ ጤፍና በቆሎ 7 ሺህ 130 ኩንታል ምርት መሰብሰቡን ገልጸዋል። የሰብል ልማቱ ቡሳ ጎኖፋ ራሱን ችሎ ለማልማት እየተንቀሳቀሰ እንዳለና ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመቋቋም ታሳቢ ያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። ምስራቅ ቦረና በተደጋጋሚ በድርቅ የሚጠቃ ቆለማና ዝናብ አጠር በመሆኑ አብዛኛው የአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ በእንስሳት እርባታና ውጤቶቹ እንደሚተዳደር አስታውሰዋል። በመሆኑም የተፈጥሮ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመቋቋምና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከዘንድሮ ሰብል ልማት ልምድና ተሞክሮ መወሰዱን ተናግረዋል፡፡ ጽህፈት ቤቱ ሰውሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመቋቋም በዞኑ ከ481 ሺህ በላይ አባላት ማፍራት መቻሉንም አክለዋል። በተያዘው በጀት አመት ከ179 ሚሊዮን ብር በላይ ሀብት በማሰባሰብ ድርቅና መሰል ችግሮችን በራስ አቅም ለመቋቋም ወደ ስራ መገባቱንም ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም እስካሁን ድረስ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ብቻ ከአባላትና ደጋፊዎቹ ከ48 ሚሊዮን ብር በላይ ሀብት በጥሬ ገንዘብ መሰብሰቡንም አክለዋል። ከአባላቱ መካከል የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪ አቶ ነጋሽ ሀይሉ ለኢዜአ እንደገለጹት በራስ አቅም ችግሮችን ለመቋቋም እየተደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታና የሚደግፉት ነው። ካለፈው አመት ጀምሮ እስካሁን የጉልበትና የጥሬ ገንዘብ ድጋፍ በማድረግ ላይ እንደሆኑም ተናግረዋል። የዚሁ ከተማ ነዋሪ አቶ ገመቹ ገቢሳ በበኩላቸው ቡሳ ጎኖፋ አንድነትንና አብሮነትን የሚያጠናክር በጎ ተግባር እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ የተፈጥሮ አደጋ ባጋጠመ ቁጥር ከእርዳታ ጠባቂነት በመላቀቅ በራስ እቅም ችግሮችን ለመፍታት የሚደረገውን ጥረት ማገዝ ከሁላችንም ይጠበቃል ብለዋል።    
ኢትዮጵያ ቅድሚያ የምትሰጣቸው የልማት ጉዳዮች ከአውሮፓ ህብረት የግሎባል ጌትዌይ ስትራቴጂ ትኩረት ጋር ይጣጣማል
Sep 1, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ቅድሚያ የምትሰጣቸው የልማት ጉዳዮች ከአውሮፓ ህብረት የግሎባል ጌትዌይ ስትራቴጂ ትኩረት ከሆኑት የንጹህ ኢነርጂ፣ የዲጂታል ትስስር፣ የግብርና እሴት ሰንሰለት እና የመሠረተ ልማት ጋር ሙሉ በሙሉ እንደሚጣጣሙ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዲማ ኖጎ (ዶ/ር) ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት በኢትዮጵያ ከአውሮፓ ህብረት ልዑክ ጋር በመተባበር “ስልታዊ አጋርነት ለለውጥ፡ የአውሮፓ ህብረት ግሎባል ጌትዌይ እና የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ” በሚል መሪ ሀሳብ የምክክር መድረክ እያካሄደ ይገኛል።   የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዲማ ኖጎ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንደገለፁት፤ ዘላቂ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን በኢትዮጵያውያን ባለቤትነት በመመራት በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ በኩል በርካታ መዋቅራዊ ለውጦች ተደርገዋል። በዚህም የውጭ ምንዛሪ ማሻሻያ፣ የፊስካል ዲሲፕሊንን ማጠናከር እና ቀደም ሲል ለውጭ ውድድር ዝግ ሆነው የቆዩ ዘርፎችን ክፍት ማድረግን ጨምሮ መንግስት ከባድ ነገር ግን አስፈላጊ ውሳኔዎችን መውሰዱን ገልጸዋል።   የአውሮፓ ህብረት የግሎባል ጌትዌይ ስትራቴጂ በንጹህ ኢነርጂ፣ በዲጂታል ትስስር፣ በግብርና እሴት ሰንሰለት እና በመሠረተ ልማት ላይ ትኩረት ማድረጉ ከኢትዮጵያ ሀገራዊ የልማት ቅድሚያዎች ጋር ሙሉ በሙሉ እንደሚጣጣም አብራርተዋል። ይህም በተቋማት አቅም ግንባታ እና ለሁለቱም ወገን በሚጠቅሙ መርሆዎች ላይ የተመሠረተ እንዲሆን ያደርገዋል ብለዋል።   የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር መሐመድ ራፊ አባራያ በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ እና በአውሮፓ ህብረት መካከል ያለው የረጅም ጊዜ ታሪካዊ እና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጎለበተ መምጣቱን ገልጸዋል። የአውሮፓ ህብረት የግሎባል ጌትዌይ ማዕቀፍ በተለይም በዘላቂ መሠረተ ልማት፣ በንጹህ ኢነርጂ፣ በዲጂታል ትስስር፣ በግብርና-ምግብ እሴት ሰንሰለት እና በሰው ሀብት ልማት ላይ የሚሰጠው ትኩረት ከሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ ጋር በእጅጉ እንደሚጣጣም አስረድተዋል። ይህ የግሎባል ጌትዌይ ማዕቀፍ የፋይናንስ እና ኢንቨስትመንት ማስገኘት ብቻ ሳይሆን፣ የተቋማትን አቅም ለማጠናከር፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማስፋፋት እና የሀገሪቷን የረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ለመደገፍ ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥርም ተናግረዋል። መድረኩ ከሀሳብ ልውውጥ ባለፈ ሁለቱ ወገኖች የጋራ ጉዳዮች በመለየት ወደ ተጨባጭ የልማት ፕሮጀክቶች እና የኢንቨስትመንት ስራዎች የሚሸጋገሩበትን መንገድ የሚያመላክት ተግባራዊ ምክረ-ሐሳብ እንደሚያፈልቅ እምነታቸውን ገልጸዋል።
በኦሮሚያ ክልል ከከተሞች ምስረታ ጋር ተያይዞ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ያደረጉ ውጤታማ ስራዎች ተከናውነዋል
Sep 1, 2026 156
ሸገር ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ) ፦ የኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ከከተሞች ምስረታ ጋር ተያይዞ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ለማድረግ ባከናወናቸው ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤቶች እየተመዘገቡ መሆኑ ተገለጸ። የሸገር ከተማ የገበሬዎች ቀን "የገበሬው እና የዘመናዊ ከተማ ግብርና፡ ለአጠቃላይ ብልፅግና" በሚል መሪ ቃል በሱሉልታ ክፍለ ከተማ በተለያዩ ሥነ-ሥርዓቶች እየተከበረ ይገኛል። ከዚህ ቀደም በከተሞች መስፋፋት እና እድገት ምክንያት በከተሞች ዙሪያ የሚኖሩ አርሶ አደሮች ተጎጂ ሆነው ቆይተዋል። በመደመር እሳቤው ግን የፌደራል እና የክልል መንግሥታት ከተሞች የአካባቢውን አርሶ አደሮች ተጠቃሚ የሚያደርጉ የተለያዩ ኢኒሼቲቮችን በመቅረጽ ባከናወኑት ሥራ አበረታች ለውጦች ተመዝግበዋል።   የሸገር ከተማም ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ አርሶ አደሩን ያካተተ እና የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ልዩ ትኩረት በመስጠት እየሠራ ያለ ሲሆን፣ በርካታ ለውጦችም እየተመዘገቡ መጥተዋል። በዚሁ መሠረት በዛሬው ዕለት የሸገር ከተማ የገበሬዎች ቀን "የገበሬው እና የዘመናዊ ከተማ ግብርና፡ ለአጠቃላይ ብልፅግና" በሚል መሪ ቃል በተለያዩ ሥነ-ሥርዓቶች እየተከበረ ይገኛል። አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ የባዛር እና ኤግዚቢሽን ፕሮግራም የተዘጋጀ ሲሆን፣ የግብርና ምርቶችም በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረቡ ይገኛሉ።   የዚህ መርሃግብር ዋነኛ ግብ ከተሞች በከተማ ግብርና በስፋት በመሰማራት በምግብ ራስን ከመቻል ባሻገር፣ ትኩስ የግብርና ምርቶችን በበቂ መጠንና በፍትሐዊ ዋጋ ለገበያ በማቅረብ የኑሮ ውድነትን መቀነስ እና ገበያውን ማረጋጋት እንደሆነ ተገልጿል። በመርሃግብሩ የሸገር ከተማ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ(ዶ/ር) እና የኦሮሚያ ክልል ከተማ እና ቤት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መሐመድ ጉዮን ጨምሮ ሌሎች የመንግስት የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል።
የክልሉን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶችን ለማከናወን ታቅዶ ወደተግባር ተገብቷል - ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን
Sep 1, 2026 133
አሶሳ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶችን ለማከናወን ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን ገለጹ። የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን የታማኝ ግብር ከፋዮች እውቅናና የታክስ ንቅናቄ መርሃ ግብር አካሂዷል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን ግብር የሀገር ህልውና ማረጋገጫ እና የልማት ሥራዎች ማሳለጫ ሞተር መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ የግብር አሰባሰብ ሂደቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ ቢመጣም ይህን አጠናክሮ ለማስቀጠል ክልሉ ያለውን የኢንቨስትመንት አማራጮች ወደ ሥራ በማስገባት የገቢ አቅምን ማሳደግ ይገባል ብለዋል። በክልሉ በገቢ ላይ የሚስተዋሉ ብልሹ አሰራሮችን ለማስተካከል መመሪያዎችን ከማሻሻል ጀምሮ የግብር ከፋዮችን ግንዛቤ የማሳደግ ሥራ እየተከናወነ መሆኑንም አመልክተዋል። በክልሉ የከተማና የገጠር ኮሪደር ልማትን ጨምሮ የተለያዩ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ ልማትን በማፋጠን የህዝብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ገቢን ማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም በተያዘው በጀት ዓመተም ከክልሉ የሚሰበሰበውን የገቢ አቅም አሟጦ በመሰብሰብ ትልልቅ የልማት ሥራዎችን ለማከናወን ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል። የግብር አሰባሰብ ሂደቱን ከብልሹ አሰራር ለማላቀቅ እና ለማዘመን የሚያግዙ ዲጂታል አሰራሮችን መተግበር መጀመሩን ገልጸው፣ በተለይም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዘርፉ በስርዓት እንዲመራ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል።   የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ተፈሪ አበበ በበኩላቸው እንዳሉት፣ ክልሉ በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት የገቢ ዕቅዱን ሙሉ ለሙሉ አሳክቷል። ክልሉ በ2025 ዓ.ም የራሱን ወጪ በራሱ አቅም ለመሸፈን ማቀዱን ገልጸው፤ በተያዘው በጀት ዓመትም 15 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ብለዋል። በተመሳሳይ የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ በ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና በታዩ ክፍተቶች ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር መክሯል።
የግብፅ የውኃ አጠቃቀምና አያያዝ ለከፍተኛ ብክነት የተጋለጠ ነው -አቶ ፈቅ አህመድ ነጋሽ
Sep 1, 2026 239
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦ የግብፅ የውኃ አጠቃቀምና አያያዝ ለከፍተኛ ብክነት የተጋለጠ መሆኑን የቀድሞ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የሦስትዮሽ ድርድር ቡድን አባል እና የውኃ ሀብት ተመራማሪው አቶ ፈቅ አህመድ ነጋሽ ገለጹ። አቶ ፈቅ አህመድ ነጋሽ የውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የድንበር ተሻጋሪ ውኃዎች እና የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ (GERD) አማካሪ ቡድን ሰብሳቢ፣ እንዲሁም የምሥራቅ ናይል አህጉራዊ የቴክኒክ ኮሚቴ ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ናቸው። የውኃ ሀብት ተመራማሪው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የኢትዮጵያ ተራራማና ጥልቅ ሸለቆዎች ውኃን ለማከማቸት እጅግ ምቹ መሆናቸውን ገልጸዋል። ውኃን በእነዚህ ቀዝቃዛ አካባቢዎች ማከማቸት ለአባይ ተፋሰስ ሀገራት የሚጠቅም መሆኑንም አመልክተዋል። ይህንን ሁኔታ በግብፅ ከሚገኘውና በበረሃማ አካባቢ በመገንባቱ ከፍተኛ የውኃ ትነት ከሚያጋጥመው የአስዋን ግድብ ጋር በማነጻጸር አቅርበውታል። በአስዋን ግድብ በዓመት ብቻ ከ15 እስከ 16 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውኃ እንደሚተንና እንደሚባክን ነው ያነሱት። ውኃን በኢትዮጵያ ጥልቅ፤ ጠባብ ሸለቆዎች ውስጥ እና አመቺ የአየር ንብረት ባለበት አካባቢ ማከማቸት የትነት መጠንን ለመቀነስ እንደሚያስችልም አስረድተዋል። ዋናው የውኃ ማከማቻ በኢትዮጵያ መሆኑ በሙቀት ሊባክን የሚችለውን በርካታ መጠን ያለው ውኃ ከማዳኑም በላይ፣ ወደ ታችኛው ተፋሰስ ሀገራት የሚለቀቀውን የውኃ መጠን አስተማማኝና የተረጋጋ እንዲሆን ያደርገዋል ሲሉ ገልጸዋል። እ.ኤ.አ በ2005 በግብፅ ከባድ የጎርፍ አደጋ በደረሰበት ወቅት የሀገሪቷ መሐንዲሶች 'ዌስተርን ስፒልዌይ' የተባለውን መስመር በመክፈት በቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር የሚለካ ውኃ ወደ ቱሽካ ሸለቆ አቅጣጫ እንዲቀይር ማድረጋቸውን አውስተዋል። ይህም የኢትዮጵያ ውኃ የማከማቸት አቅም በከፍተኛ ሁኔታ መጨመር በተፋሰሱ ላይ ያለውን ከመጠን ያለፈ የውኃ ብክነት ለመቀነስና የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት መሠረተ ልማቶች ለጎርፍ አደጋ እንዳይጋለጡ ለመከላከል እንደሚቻል ማሳያ ነው ብለዋል። በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ተራራማ ሸለቆዎች የሚከማቸው ውኃ መጨመር በግብፅና ሱዳን በኩል በየዓመቱ የሚባክነውን አጠቃላይ የውኃ መጠን በከፍተኛ ሁኔታ መቀነስ እንደሚያስችልም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የውኃ ማከማቻዎች ጥቅም በውኃ ጥበቃ ብቻ የተወሰነ አለመሆኑንም የውኃ ሀብት ተመራማሪው ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የሃይድሮ ኤሌክትሪክ መሠረተ ልማቶች ከሀገር ውስጥ ፍላጎት አልፈው ንጹሕና በተመጣጣኝ ዋጋ የኤሌክትሪክ ኃይል የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት እንዲያገኙ የሚያስችል ዕድል እንደሚፈጥር ነው ያሉት። እንዲህ ዓይነት የኢነርጂ ትብብር በናይል ተፋሰስ ሀገራት መካከል ላለው የኢኮኖሚ ትብብር ተጨማሪ አቅም እንደሆነም አንስተዋል። ከእነዚህ ሁለገብ ጥቅሞች ተጠቃሚ ለመሆን በናይል ወንዝ ላይ በጋራ ተጠቃሚነትና መተማመን ላይ የተመሠረተ ጠንካራ ትብብር ሊፈጠር እንደሚገባ አቶ ፈቅ አሳስበዋል።
በአማራ ክልል የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ አበረታች ውጤት እያስመዘገበ ነው
Sep 1, 2026 112
ጎንደር፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ እና የሥርዓተ-ምግብ ችግርን በመቅረፍ ረገድ አበረታች ውጤት ማስገኘቱን የአማራ ክልል እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊዎችና ባለሙያዎች የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ያለበትን ደረጃ እና በምርት አቅርቦት ረገድ እያስገኘ ያለውን ውጤት በጎንደር ከተማ ተዘዋውረው ጎብኝተዋል። የቢሮው የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሀብታሙ ሁነኛው በጉብኝቱ ወቅት እንደገለጹት፤ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የሥርዓተ-ምግብን ለማሻሻል የሌማት ትሩፋትን በስፋት የመተግበር ሥራ እየተከናወነ ይገኛል። መርሃ ግብሩ በቂ ምርት ለማቅረብ፣ ለወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠርና የኑሮ ውድነትን ለማቃለል የሚያስችል ውጤት ማስገኘቱንም ገልጸዋል። በተጠናቀቀው የበጀት ዓመትም ከ1 ነጥብ 6 ቢሊየን በላይ እንቁላል፣ ከሁለት ነጥብ ሰባት ሚሊዮን ቶን በላይ ወተት እና 900 ሺህ ቶን የሥጋ ምርት በማምረት ለገበያ ማቅረብ መቻሉን በማሳያነት አንስተዋል። በተጨማሪም ከ36 ሺህ ቶን በላይ ማር በማምረት ለገበያ ማቅረብ መቻሉን ጠቁመው፤ የዓሣ ልማቱንም በሐይቆች፣ በወንዞች እና በሰው ሠራሽ ኩሬዎች ጭምር በማስፋት አበረታች ውጤት መመዝገቡን አስረድተዋል። ለሌማት ትሩፋት ማነቆ የነበረውን የመኖ እጥረት በዘላቂነት ለመቅረፍም 46 ዘመናዊ የመኖ ማቀናበሪያ ፋብሪካዎችን ወደ ማምረት ማስገባት መቻሉንም ጠቅሰዋል። በከተሞችና አካባቢው በስፋት እየተካሄደ የሚገኘውን የሌማት ትሩፋት በቀጣይም በሁሉም የገጠር አካባቢዎች ለማስፋት የልምድ ልውውጥ እየተደረገ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል። በጎንደር ከተማ አስተዳደር እንስሳትና ዓሣ ሀብት መምሪያ የኤክስቴንሽን ኮሙኒኬሽን ባለሙያ አቶ ሀብታሙ ዘገዬ ፤ ተግባራዊ የተደረገው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በየዘርፉ ውጤት ተገኝቶበታል ብለዋል። በዘርፉ ተደራጅተው ወደ ሥራ ለገቡ ወጣቶች የብድር፣ የቦታ እና ሌሎች ድጋፎችን በመስጠት የከተማውን የእንቁላል፣ የወተትና የሥጋ አቅርቦት እጥረት በአጭር ጊዜ ማሻሻል መቻሉን አስረድተዋል። ለመጪው የአዲስ ዓመት በዓልም ከ65 ሺህ በላይ የሥጋ ዶሮ፣ 40 ሺህ የደለበ በግና ፍየል በማቅረብ ገበያውን ለማረጋጋት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አረጋግጠዋል። በከተማው በዶሮና ንብ እርባታ የተሰማሩት ወይዘሮ ፅላተማርያም ተመስገን እንደተናገሩት፤ በ50 ጫጩቶች የጀመሩት የዶሮ እርባታ ሥራ ከፍተኛ ውጤት ማስገኘቱን ገልጸዋል። በአሁኑ ሰዓትም በሦስት ቅርንጫፎች 47 ሺህ እንቁላል ጣይ ዶሮዎችን በማራባት በቀን እስከ 27 ሺህ የሚደርስ እንቁላል ለገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የከተማ አስተዳደሩ ባደረገላቸው ድጋፍ የንብና የዓሣ ልማትን በተቀናጀ አግባብ መጀመራቸውን አመልክተው፤ በተሰማሩበት መስክም ለ137 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም ተናግረዋል። የ"ዘርፌ፣ ሀና እና ጓደኞቻቸው" ሽርክና ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ሽመልስ አርጋው በበኩላቸው፤ በ45 ሺህ ብር የጀመሩትን የወተት ልማት ስራ ላይ ጠንክረው በመሥራት ውጤታማ መሆን መቻላቸውን አመልክተዋል።
አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የመዲናዋ የአመራር አባላት በቁርጠኝነት ሊተጉ ይገባል
Aug 31, 2026 328
አዲስ አበባ ፣ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የመዲናዋ የአመራር አባላት በቁርጠኝነት ሊተጉ እንደሚገባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት እና በ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ ላለፉት ሁለት ቀናት ሲያካሂድ የነበረውን ውይይት አጠናቋል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በውይይቱ ማጠቃለያ ባስተላለፉት የሥራ መመሪያ፤ መዲናዋን የብልጽግና ተምሳሌት የሚያደርጉ ተጨባጭ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   ፕሮጀክቶችን በጥራት፣ በፍጥነትና በተሻለ አቅም የመፈጸም ልምድ እየጎለበተ መሆኑን ገልጸው፤ በውጤታማ የሀብት አጠቃቀም የተመደበው ገንዘብ ለታለመለት ዓላማ በማዋል የተሻለ አፈፃፀም ተመዝግቧል ብለዋል። የሙሉ ቀን ሥራ ባህል እየሆነ መምጣቱን በማንሳት፤ ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመለወጥ ዜጎቸን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥል ገልጸዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር ገቢራዊ በማድረግ በመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚስተዋለውን የመልካም አስተዳደር ችግር በዘላቂነት መፍታት የሚያስችል ውጤት ተገኝቷል ብለዋል። በንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት፣ በመንገድ፣ በጤና፣ ትምህርት፣ የስራ ዕድል ፈጠራ፣ በወንዝ ዳርቻዎችና ኮሪደር ልማት ህዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሥራዎቸን ለማከናወን ዕቅድ መያዙን ገልጸዋል። በመሆኑም አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የመዲናዋ የአመራር አባላት በቁርጠኝነት ሊተጉ ይገባል ብለዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ እና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ጃንጥራር ዓባይ በበኩላቸው፤ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተያዙ ዕቅዶችን ለማሳካት የአመራር አባላት የጋራ ግንዛቤ በመያዝ የለውጥ ርምጃዎችን መጀመር እንዳለባቸው ገልጸዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ዲሞክራሲ ስርዓት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ እንዳሉት፣ህዝቡ በምርጫው የሰጠንን ተጨማሪ ዕድል በልማት ለመካስ ለቀጣይ ተልዕኮ ራሳችንን ማዘጋጀት ይገባናል ብለዋል።
በአማራ ክልል ከአምስት ነጥብ ስድስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ተሸፍኗል
Aug 31, 2026 117
ባህርዳር፣ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ) ፡-በአማራ ክልል በተያዘው የመኸር ወቅት የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ከአምስት ነጥብ ስድስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መሸፈን መቻሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። የቢሮው የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማደፍሮ አስላከ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በ2018/19 የምርት ዘመን በምግብ ራስን ከመቻል ያለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት እየተሰራ ነው። በምርት ዘመኑ ከአምስት ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት የእንክብካቤ ስራ ማከናወን እየተካሄደ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   አጠቃላይ ከለማው መሬት ውስጥ ከአንድ ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በዘመናዊ ትራክተር በማረስ ማልማት መቻሉንም አመልክተዋል። ከሶስት ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ የሚሆነውን መሬት ደግሞ በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ የለማ መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩ ሰብሉን የማረም፣ የመኮትኮትና ከተባይና ከበሽታ በመከላከል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ለዚህ የምርት ዘመንም አምስት ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ዘመናዊ የአፈር ማዳበሪያን ጨምሮ 524 ሺህ ኩንታል የተለያየ ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ መዋሉን አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅት ያለው አፈጻጸም በምርት ዘመኑ ይገኛል ተብሎ የታቀደውን ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ አጠቃላይ ምርት ለማሳካት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የወንበርማ ወረዳ አርሶ አደር ቸኮል ታደለ፤ አራት ሄክታር መሬታቸውን በኩታ ገጠም አስተራረስና በትራክተር በማረስ በቆሎና ስንዴ መዝራታቸውን ገልጸዋል። በባለሙያዎች ምክረ ሃሳብ በመታገዝ የማዳበሪያና የምርጥ ዘር ግብዓት ተጠቅመው ያለሙት ሰብል እድገቱና ቁመናው በተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ከሁለት ሄክታር በላይ መሬታቸውን በወቅቱ በዘር ሸፍነው እየተንከባከቡ እንደሚገኙ የገለጹት ደግሞ በሰሜን ጎጃም ዞን የጎንጅ ቆለላ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አለምነው ደሴ ናቸው። እያለሙት ያለው ጤፍና የበቆሎ ሰብል በጥሩ ቁመና ላይ የሚገኝ በመሆኑ የተሻለ ምርት አገኛለሁ ብለው እየሰሩ መሆናቸውን ነው የጠቀሱት። በ2017/2018 የምርት ዘመን በክልሉ ከለማው አምስት ነጥብ አምስት ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ከ188 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ማምረት መቻሉን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።  
ሕብረተሰቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ልምዱን በማሳደግ አምራቹን ማበረታታት አለበት - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Aug 31, 2026 104
ሃዋሳ፤ ነሐሴ 25/2018(ኢዜአ)፡-ሕብረተሰቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ልምዱን በማሳዳግ በአምራች ዘርፍ የተሰማሩ ባለሀብቶችን ማበረታታት እንዳለበት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ አስታወቁ። የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ''የኢትዮጵያን ይግዙ'' በሚል መሪ ሃሳብ በሀዋሳ ከተማ የተዘጋጀውን የንግድ አውደ ርዕይና ባዛር ከፈተዋል።   በንግድ አውደ ርዕዩና ባዛሩ የቀረቡ ምርቶችን ተዘዋውረው የተመለከቱ ርዕሰ መስተዳድሩ ህብረተሰቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ባህሉን እንዲያሳድግ ጠይቀዋል። የንግድ ሳምንቱ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት የተረጋጋ የግብይት ሥርዓት እንዲፈጠር አጋዥ መሆኑንም ገልጸዋል። ማህበረሰቡ በአምራች ኢንዱስትሪ መስክ የተሰማሩ ባለሀብቶችን ለማገዝና የሀገር ኢኮኖሚን ለመደገፍ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመግዛትና የመጠቀም ልምዱን ማጎልበት እንዳለበት አስገንዝበዋል። የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ሃላፊዋ ወይዘሮ ሰላማዊት መኩሪያ በበኩላቸው እንዳሉት አውደ ርዕይና ባዛሩ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ባህልን በማሳደግ ኢኮኖሚያዊ አቅምን ለማጠናከር ያለመ ነው፡፡ በአውደ ርዕዩና ባዛሩ ላይ ቁጥራቸው 168 የሚሆኑ አምራቾች፣ ነጋዴዎች፣ ዩኒየኖች፣ ላኪዎች፣ አገልግሎት ሰጪዎችና በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ላይ የሚሳተፉ ማህበራት ጭምር መሳተፋቸውን ገልጸዋል፡፡   በዚህም መጪዎቹን በዓላት ታሳቢ ያደረጉ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ገበያን የማረጋጋት ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አውደ ርዕይና ባዛሩ ዘላቂ የገበያ ትስስር በመፍጠር በኢኮኖሚ እንቅስቃሴው ላይ ከፍተኛ ፋይዳ ያለው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በአውደ ርዕይና ባዛሩ ላይ ምርታቸውን ካቀረቡት መካከል የሲዳማ ዶና ህብረት ሥራ ዩኒየን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ገነነ ልኡልሰገድ የአትክልና ፍራፍሬ ምርቶችን ይዘው መቅረባቸውን ገልጸዋል። ከ5ሺህ በላይ አባላት የሚሰበስቧቸውን ምርቶችን በተሻለ የገበያ አማራጭ በማቅረብ ገበያን ከማረጋጋት ባለፈ የአባላቱን የገቢ አቅም እያሳደጉ መሆኑን ገልጸዋል። "የኢትዮጵያን ይግዙ" የንግድ አውደ ርዕይና ባዛር የገበያ ትስስር የሚፈጥር ምቹ አጋጣሚ በመሆኑ የአካባቢውን ምርት በሚገባ ለማስተዋወቅ እንደሚጠቀሙበት ገልጸዋል። የብራውን ፉድ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ድርጅት ተወካይ አቶ መርዕድ ጋሹ የንግድ አውደ ርዕይና ባዛሩ ምርቶቻቸውን በማስተዋወቅ የተሻለ የገበያ ትስስር እንደሚፈጥሩበት ገልጸዋል። የንግድ አውደ ርዕዩና ባዘሩ እስከ ጳጉሜን 3 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚቆይ በስነስርዓቱ ላይ ተገልጿል።
ታይላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ስትራቴጂካዊ ግንኙነት ማጠናከር ትፈልጋለች
Aug 31, 2026 302
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ታይላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ስትራቴጂካዊ ትብብር ለማጠናከር እና ከአፍሪካ አህጉር ጋር ያላትን አጋርነት ለማስፋት ፍላጎት እንዳላት የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉአንግኬትኪኦ ገለጹ። የታይላንድ የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉአንግኬትኪኦ በኢትዮጵያ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት አድርገዋል። ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ አዲስ አበባ በደቡብ ምስራቅ እስያ እና በአፍሪካ መካከል ዋና የትስስር ድልድይ ሆና እየወጣች መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ከታይላንድ ጋር የቆየ ታሪካዊ ግንኙነት ያላት ሀገር መሆኗን አንስተው፤ ሀገራቸው ይህንን ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እና ሁለንተናዊ ትብብሯን ለማሳደግ እንደምትሠራ አስታውቀዋል። በተለይም በኢንዱስትሪ ልማት እና በግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመር ረገድ ያላትን መልካም የልማት ተሞክሮ ለኢትዮጵያ ለማካፈል ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል። የጉብኝታቸው ዋና ዓላማም ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ታሪካዊ የሁለትዮሽ ግንኙነት ማጠናከር እና መቀመጫነቱ አዲስ አበባ ከሆነው የአፍሪካ ኅብረት ጋር ያለውን ተሳትፎ ማሳደግ እንደሆነ አብራርተዋል። በዚህም ታይላንድ በአዲስ አበባ ኤምባሲዋን ለመክፈት መወሰኗን ጠቁመዋል፡፡ ሀገራቸው በአፍሪካ ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ተጽዕኖ ለማጠናከር እና አዲስ አበባን የመላው አህጉራዊ ግንኙነቷ ዋና ማዕከል ለማድረግ የምታደርገውን ጥረት የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ሀገራቸው ከአፍሪካ ጋር ያላትን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ እና የልማት አጋርነት ለማሳደግ ያለመውን "የታይላንድ-አፍሪካ ተነሳሽነት" የተሰኘ መርሃ-ግብር በልዩ ትኩረት እየተገበረች እንደምትገኝ ገልጸዋል። ሚኒስትሩ የአፍሪካ አህጉር ፈጣን ዕድገት በማስመዝገብ ላይ እንደምትገኝ ጠቅሰው፤ አሁን ላይ አፍሪካ በዓለም አቀፍ ደረጃ በደቡቡ የዓለም ክፍል (Global South) ውስጥ ጠንካራ እና ተጽዕኖ ፈጣሪ ድምፅ ሆና መውጣቷን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የደቡቡ የዓለም ክፍል በዓለም አቀፍ መድረክ ያለው ተጽዕኖ እንደሚያመላክት ጠቅሰው፤ የታይላንድ ዋና ዓላማም ከዚሁ እውነታ ጋር የተጣጣመ አህጉራዊ አጋርነት መገንባት መሆኑን ገልጸዋል። ከነባርና ከአዳዲስ የአፍሪካ ሀገራት ጋር በጋራ በመሥራትም ቀደም ሲል ከተመዘገቡት ስኬቶች በላይ በርካታ የጋራ ውጤቶችን ማስመዝገብ እንደሚቻል እምነታቸውን ተናግረዋል። አዲስ አበባ የአሴአን (ASEAN) እና የአፍሪካ ዋና የትስስር ማዕከል መሆኗን የጠቆሙት ዲፕሎማቱ፤ ኢትዮጵያና ታይላንድ በአፍሪካ ኅብረትና በአሴአን መካከል ጠንካራ የትብብር ድልድይ በመገንባት ከፍተኛ ሚና መጫወት እንደሚችሉ ገልጸዋል። በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በከፍተኛ አመራሮች ደረጃ የሚደረጉ የጋራ ጉብኝቶችና ተደጋጋሚ ውይይቶች ወሳኝ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ሚኒስትሩ ታይላንድ እና የአፍሪካ ሀገራት ሕግን መሠረት ያደረገውን ዓለም አቀፍ ሥርዓት ለማስጠበቅ፣ ነፃ ንግድን ለማስቀጠል እና በዓለም የንግድ ድርጅት (WTO) ሥር ያለውን የንግድ ሥርዓት ለማጠናከር በጋራ መሥራት እንዳለባቸው አሳስበዋል። የኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል መሆንም ከዓለም አቀፍ የንግድ ሕጎች እና ኢኮኖሚ ጋር በንቃት እንድትሳተፍ የሚያበረታታ መሆኑን አብራርተዋል።
በክልሉ በመንገድና ትራንስፖርት ልማት ዘርፍ የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ አበረታች ሥራዎች ተከናውነዋል
Aug 31, 2026 88
ወልቂጤ፣ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ):-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በመንገድና ትራንስፖርት ልማት ዘርፍ የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ አበረታችሥራዎች መከናወናቸውን የክልሉ መንገድና ትራንስፖርት ልማት ቢሮ አስታወቀ። ከክልሉ፣ ከዞኖችና እና ልዩ ወረዳ የመጡ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በትራንስፖርትና መንገድ ልማት ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ ዛሬ በወልቂጤ ከተማ ተካሂዷል።   በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪ እና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ሃላፊ መሀመድ ኑርዬ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ለትራንስፖርት እና ለመንገድ ልማት ሥራዎች በተሰጠ ትኩረት ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረገ አበረታች ውጤት ተገኝቷል። በተለይ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዘርፉ የክልሉን ህዝብ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተከናወኑ ሥራዎች በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸውን ነው ያመለከቱት። በዘርፉ የተከናወኑ እነዚህ ተግባራት የሕዝብን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ከማቀላጠፍ ባለፈ ለክልሉ ሁለንተናዊ ዕድገት መጠናከር ወሳኝ ሚና እንዳላቸውም አስረድተዋል። በመናኸሪያዎች የኢ-ትኬቲንግ አሰራርና ሌሎች የሪፎርም ሥርአቶችን ከመዘርጋት ባለፈ በትራንስፖርት አገልግሎት ላይ ጠንካራ ቁጥጥርና የህግ ማስከበር ሥራ መሰራቱ ለውጥ አምጥቷል ብለዋል። ​እንደ ቢሮ ሀላፊው ገለጻ በክልሉ የትራንስፖርት አቅርቦት እጥረት በነበረባቸው አካባቢዎች አዳዲስ የሕዝብ ትራንስፖርት ስምሪቶችን በማስጀመር የኅብረተሰቡን ጥያቄዎች ለመመለስ ተችሏል። የተቀናጀ የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሠራሮች በመዘርጋታቸውም የትራፊክ አደጋን መቀነስ አስችሏል ብለዋል። እንደ መሀመድ (ዶ/ር) ገለጻ ​በመንገድ መሰረተ ልማት አዳዲስ የመንገድ ፕሮጀክቶችን ከመገንባት ባለፈ የነበሩትን በመጠገንና ደረጃቸውን በማሻሻል የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በመንግስትና በህብረተሰቡ ተሳትፎ 52 የመንገድ ፕሮጀክቶች ለመገንባት መቻሉን ነው የገለጹት። መንግስት አርሶ አደሩን፣ ባለሀብቱንና የአካባቢውን ተወላጆች በማስተባበር የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያከናውናቸው ተግባራት በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የጉራጌ ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ናስር ሃሰን በበኩላቸው እንዳሉት በዞኑ በህብረተሰብ ተሳትፎ የመንገድ ከፈታና የድልድይ ግንባታ ፕሮጀክት ሥራዎች ተከናውነዋል። ለአገልግሎት የበቁት እነዚህ ፕሮጀክቶች ለዓመታት ከህዝብ ሲነሱ የነበሩ ቅሬታና የልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ ማስቻላቸውን ተናግረዋል። በመደመር መንግስት ህዝብን በማሳተፍ የሚሰሩ የልማት ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።
በጋምቤላ ክልል ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ኢንሼቲቭን ስኬታማ ለማድረግ የባለድርሻ አካላት አስተዋጾ እንዲጠናከር ተጠየቀ
Aug 31, 2026 204
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 25/ 2018 (ኢዜአ)፡-በጋምቤላ ክልል ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ኢንሼቲቭን ስኬታማ ለማድረግ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎና ትብብር ሊጠናከር እንደሚገባ ተገለፀ። በብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ላይ ያተኮረ እና የዘርፉ ተመራማሪዎችና ባለሙያዎች የተሳተፉበት የውይይት መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተካሂዷል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አድሮው ቱት በውይይት መድረኩ ላይ እንዳሉት መንግስት የግብርናን ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል።   በተለይም የፍራፍሬ ልማት በገበያ ተፈላጊነቱ እየጨመረ መምጣቱን ጠቅሰው፣ ይህም የአርሶ አደሮችን ገቢ በማሳደግ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። እንደ ሀገር ተግባራዊ መደረግ የጀመረው ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ኢኒሼቲቭ በፍራፍሬ ልማት ዘርፍ የታለመውን ግብ ለማሳካት አበርክቶው የላቀ ነው ብለዋል። ኢኒሼቲቩ በክልሉም ተግባራዊ መደረግ መጀመሩን ገልጸው፣ ስኬታማ እንዲሆንም የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ወሳኝ ሚና እንዳለው ገልፀዋል።   በክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ የብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ አብርሃም ኡቻላ በበኩላቸው በክልሉ ለአቮካዶ ልማት ምቹ ስነ-ምህዳር ባላቸው የጎደሬና የመንገሺ ወረዳዎች ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም መጀመሩን ተናግረዋል። በነዚሁ ወረዳዎች የአቮካዶ ልማቱን በማስፋትና ለአርሶ አደሩ በማስተዋወቅ ምርታማቱን እንዲያሳድግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። መድረኩ በአቮካዶ ችግኝ ልማትና የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎችን ማጠናከር፣ የአቮካዶ የድህረ ምርት አያያዝና የገበያ ትስስርን መፍጠር እንዲሁም የባለሙያዎችና የአርሶ አደሮችን ተሳትፎ ማሳደግ ላይ ያተኮረ መሆኑ ታውቋል።  
በሲዳማ ክልል የንግድ ሥርዓቱን ፍትሃዊነትና ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ሥራ ይጠናከራል
Aug 31, 2026 98
ሀዋሳ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የንግድ ስርዓቱን ፍትሃዊነትና ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ስራ እንደሚጠናከር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ከንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ጋር በመተባበር ባዘጋጀው "የኢትዮጵያን ይግዙ" የንግድ ሳምንት ላይ ያተኮረ ውይይት በሃዋሳ ከተማ እየተካሄደ ነው።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በመድረኩ ላይ እንደተናገሩት በክልሉ የንግድ ስርዓቱን ፍትሃዊነትና ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ሥራ ይጠናከራል። ለዚህም ህጋዊ አሰራሩን የማዘመን ተግባራትን በማስቀጠል ኢኮኖሚያዊ ፋይዳውን ለማጉላት ይሰራል ብለዋል። በንግድ ሥርዓት ውስጥ የሚታየውን ህገወጥነት ከመከላከል ባለፈ ግብር ከፋዩን በማበረታታት በዘርፉ ያሉ ማነቆዎችን ለመፍታት በቅንጅት እንደሚሰራም አመልክተዋል። በዚህም የማምረት አቅምን በማጎልበት በክልሉ ያሉ አስመጪና ላኪዎችን ቁጥር የማሳደግ ሥራ በትኩረት እንደሚከናወን ገልጸዋል። የሲዳማ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሰላማዊት መኩሪያ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በክልሉ የሚካሄደው የንግድ ሳምንት የሀገር ውስጥ ምርት የመጠቀም ልምድን እያሳደገ መጥቷል።   በዚህም በኢንዱስትሪና በግብርና ምርት ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎች፣ ዩኒየኖች፣ ማህበራትና ሌሎች የዘርፉ ተዋንያን የተፈጠረላቸውን የግብይት ሥርአት በመጠቀም ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል። በዘንድሮው የንግድ ሳምንት መጪዎቹን በዓላት ታሳቢ ያደረጉ ምርቶችን በማቅረብ ገበያን ከማረጋጋት ባለፈ በክልሉ የኤክስፖርት ምርት ላይ ያተኮረና በጥናት የተደገፈ ውይይት እንደሚካሄድ ገልጸዋል። በዚህም ቡናን ጨምሮ በአቮካዶና በሌሎች የኤክስፖርት ምርቶች ላይ ያለውን አቅም በመለየት የንግድና ግብይት ስርአቱን የማሳለጥ ሥራ በትኩረት ይከናወናል ብለዋል። በመድረኩ በኤክስፖርት ምርት ላይ ያተኮረ ጥናታዊ ጽሁፍ ቀርቦ ውይይት የተደረገበት ሲሆን "የኢትዮጵያን ይግዙ" በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ የንግድ አውደ ርዕይና ባዛርም ይከፈታል ተብሎ ይጠበቃል።
የማዕድን ሀብትን በዘላቂነት በማልማት እና በአግባቡ በማስተዳደር ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ማሳደግ ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን
Aug 31, 2026 78
አሶሳ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፡- የማዕድን ሀብትን በዘላቂነት ለማልማት እና በአግባቡ ለማስተዳደር የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ በየደረጃው ከሚገኙ የዘርፉ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ጋር የማዕድን ሀብትን በዘላቂነት ማልማት በሚቻልበት መስክ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ አካሂዷል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻደሊ ሀሰን፤ የማዕድን ሀብት የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በመደገፍና የውጭ ምንዛሬ በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በክልሉ የማዕድን ሀብት በስፋት እየተመረተ ቢሆንም ህገ-ወጥ እንቅስቃሴዎችን መቆጣጠርና ዘርፉን በአግባቡ ማስተዳደር እንደሚገባ አሳስበዋል። በአሁኑ ወቅትም የማዕድን ሀብትን በዘላቂነት ለማልማት እና በአግባቡ ለማስተዳደር የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ነው የጠቀሱት። የወጡ ህጎችና አዋጆች በዘርፉ የተሰማሩ አካላትን ተጠቃሚ የሚያደርጉ በመሆናቸው በአግባቡ መተግበር እንዳለባቸው ነው የጠቆሙት።   በመሆኑም ማዕድን የሚወጣባቸውን አካባቢዎች መልሶ በማልማት የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የክልሉ ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ቱጃኒ አደም በበኩላቸው፤ በክልሉ የሚገኙ የማዕድን ሀብቶችን ለይቶ በማልማት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የማዕድን ሀብት የግጭት መንስኤ እንዳይሆን የዘርፉ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት በህግ አግባብ ብቻ መንቀሳቀስ እንዳለባቸው አሳስበዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም