ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ያስመዘገበውን ለውጥ ማጠናከር ይገባል - ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ
Aug 7, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ያስመዘገበውን ለውጥ ማጠናከር እንደሚገባ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ገለጹ። ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ስር እየተካሄዱ ያሉ የአዳማ ጋርመንትና ኢንዱስትሪ፣ የጋሻ የሠራዊቱ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ፕሮጀክት እና የመከላከያ ባጅና ሜዳሊያ ማምረቻ ፋብሪካን ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ወቅት የአዳማ ጋርመንት ኢንዱስትሪ ያስገነባውን አዲስ የማስፋፊያና የማሻሻያ ፕሮጀክት መርቀው ከፍተዋል። ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በጉብኝታቸው ወቅት፣ የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን አመራሮችና ሠራተኞች ላስመዘገቡት ውጤት በማመስገን የተገኘው ለውጥ ሳያዘናጋቸው ለበለጠ ውጤት እንዲተጉ አሳስበዋል። በቀጣይም የምርት ጥራትን በማሻሻል፣ የምርምርና የቴክኖሎጂ ልማትን በማስፋፋት፣ የዲጂታላይዜሽን ሥራዎችን በማጠናከር፣ የግብዓት አቅርቦትን በራስ አቅም በማሳደግ በአፍሪካ ደረጃ ተወዳዳሪ ኢንዱስትሪ እንዲገነባ አቅጣጫ ሰጥተዋል። ሠራዊቱ መለኪያው ሀገሩ ነው ያሉት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ፣ የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን የተቋሙንና የሀገራችንን ፍላጎት በማሳካት ያለውን ሚና ይበልጥ ማጠናከር ይገባል ብለዋል። በጉብኝቱ ላይ የአዳማ ከተማ ከንቲባን ጨምሮ የመከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ አመራሮች እና የፋውንዴሽኑ የሥራ ኃላፊዎች መገኘታቸውን የመከላከያ ሠራዊት ማኅበራዊ ትሥሥር ገጽ መረጃ አመላክቷል።
በሲዳማ ክልል የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኢንዱስትሪ ልማት መስፋፋት ምቹ መደላድል ፈጥሯል
Aug 7, 2026 71
ሃዋሳ፣ ነሀሴ1/2018(ኢዜአ)፡-በሲዳማ ክልል የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኢንዱስትሪ ልማት መስፋፋት ምቹ መደላድል መፍጠሩን የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ ገለጹ። የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ የ2018 በጀት አመት አፈጻጸምና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በሃዋሳ ከተማ ተካሂዷል። በመድረኩ የተገኙት የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ እንደገለጹት በክልሉ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኢንዱስትሪ ልማት መስፋፋት ምቹ መደላድል ፈጥሯል። ይህም የኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም በማሳደግ ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባሻገር ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ የመተካት አቅምን እያሳደገ መሆኑን ጠቁመዋል። በቀጣይም የኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም ይበልጥ ለማሳደግ መስረተ ልማቶችን በቅንጅት የማሟላት ሥራው በቀጣይም ይጠናከራል ብለዋል። የክልሉ ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ አሻግሬ ጀምበሬ በበኩላቸው በክልሉ የኢንዱስትሪ አቅምን በማጠናከር የማምረት አቅምን የማሳደግ፣ የስራ ዕድል የመፍጠር፣ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን መጠን የመጨመርና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ የመተካት ሥራ በትኩረት መከናወኑን ጠቁመዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ249 በላይ አዳዲስ ኢንዱስትሪዎችን ወደ ሥራ የማስገባትና ነባሮቹን በመደገፍ ከ22 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩንም ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ ከክልሉ 14 ሺህ 500 ቶን የኢንዱስትሪ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ 155 ሚሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱንም አቶ አሻግሬ ጠቅሰዋል። በተመሳሳይ 290 ሚሊዮን ዶላር የሚገመቱ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካት ተችሏል ብለዋል።
በሲዳማ ክልል አርሶ አደሩን ከእንስሳት ልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ሆነዋል
Aug 7, 2026 61
ይርጋለም፤ ነሀሴ 1/2018 (ኢዜአ)፡-አርሶ አደሩን ከእንስሳት ልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ በመኖ አቅርቦትና ጤና አጠባበቅ ላይ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን የሲዳማ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሀም ማርሻሎ ተናገሩ። የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ የ2019 በጀት ዓመት የእንስሳት መኖ ልማትና የበሽታ መከላከያ ክትባት ሥራዎች ይፋዊ ማስጀመሪያ መርሀግብር በይርጋዓለም ከተማ ተካሂዷል። በመርሀግብሩ ላይ የሲዳማ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሀም ማርሻሎ በክልሉ የአርሶ አደሩን ከእንስሳት ልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የተከናወኑ የመኖ አቅርቦትና ጤና አጠባበቅ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። ዘመናዊ የእንስሳት እርባታ ዘዴው ለእንስሳት ዝርያ ማሻሻል፣ ለመኖ አቅርቦትና ለጤና አጠባበቅ ሥራ ከፍተኛ እገዛ ማድረጉንም ገልጸዋል። አርሶ አደሩ የመኖ አቅርቦቱን ከሌማት ቱሩፋት ሥራ ጋር በማቀናጀትና የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማነቱን ማሳደጉን ጠቁመዋል። የክልሉ መንግስት የአርሶ አደሩን ከእንስሳት ልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ ከሚያደርገው ሞያዊ እገዛ በተጨማሪ የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎችን ማቅረቡን አንስተዋል። የክልሉ እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰፋ ፎና በክልሉ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር ከመጀመሩ በፊት 170 ሺህ የነበረው የተሻሻሉ የዳልጋ ከብቶች ቁጥር በአሁኑ ወቅት ወደ 600 ሺህ ለማሳደግ መቻሉን አብራርተዋል። ይህም የክልሉን የእንስሳትና እንስሳት ተዋጽኦ ከማሳደግ ባለፈ የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት መሳደጉን አንስተዋል። ከዚህ በተጓዳኝም የእንስሳት መኖ አቅርቦትን ለማስፋት በተደረገ ጥረት በበጀት ዓመቱ ከ32 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ልማቱ መካሄዱን ጠቁመዋል። በክልሉ የእንስሳት ጤናን ለመጠበቅም የበሽታ መከላከልና ክትባት ሽፋኑንለማሳደግ በቅንጅት መሰራቱን አስረድተዋል። ይህም የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር ለማሳካትና የአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት ከማሳድግ ባለፈ ለኢንዱስትሪዎች ግብአት ለማቅረብ አስችሏል ብለዋል። በይርጋዓለም ከተማ ጋኔ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ደረጀ ሙጤ የተሻሻሉ ዝርያ ያላቸው የወተት ላሞች በማርባት ወተትና የወተት ተዋጾን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለእንስሳቱም በግማሽ ሄክታር መሬታቸው ላይ የመኖ ሣር በማልማት ውጤታማነታቸውን ለማጉላት እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። የእንስሳቱን ምርታማነት ለማሳደግ የምጥን መኖ አቅርቦትና ጤናቸውን መከታተል ላይ የባለሞያ ድጋፍ ማግኘታቸውንም ጠቁመዋል። በማስጀመሪያ መርሀ ግብሩ ላይ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደን ጨምሮ የክልል፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች የተገኙ ሲሆን በይርጋለም ከተማም የተለያዩ የሌማት ትሩፋት ስራዎች ተጎብኝተዋል።
የደጃዝማች በላይ ዘለቀ አውሮፕላን ማረፊያ አዲስ ተርሚናል የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ፍሰቱን ያቀላጥፋል
Aug 7, 2026 89
ባህር ዳር ፤ነሐሴ 1/2018(ኢዜአ)፡- የደጃዝማች በላይ ዘለቀ አውሮፕላን ማረፊያ አዲስ ተርሚናል የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ፍሰቱን እንደሚያቀላጥፍ በዘርፉ የተሰማሩ ግለሰቦች ገለጹ። በባህር ዳር ከተማ የደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በአዲስ የተገነባውን ተርሚናል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መመረቃቸው ይታወሳል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ በባህር ዳር የተገነባው ተርሚናል በኢትዮጵያ ከቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ቀጥሎ ግዙፉ ተርሚናል መሆኑን መግለጻቸው አይዘነጋም። አስተያየት ሰጪዎች እንዳሉት የአውሮፕላን ማረፊያው ተርሚናል በአዲስ መልክ መገንባቱ የከተማዋን የቱሪዝም፣ የኢንቨስትመንትና የንግድ እንቅስቃሴ ለማፋጠን ያስችላል ብለዋል። የባህር ዳር አስጎብኚዎች ማኅበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ማስተዋል ዘለቀ እንደገለጹት፤ የተርሚናሉ ዓለም አቀፍ ደረጃውን ጠብቆ መገንባት የቱሪዝም ዘርፉን ዕድገት የሚያፋጥን ነው። ባህር ዳር በጣና ሐይቅ የሚገኙ ገዳማትን፣ የጢስ አባይ ፏፏቴንና ሌሎች በውስጧ የሚገኙ የመስህብ ሀብቶችን ለመጎብኘት የሚመጡ እንግዶችን በማስተናገድ የምትታወቅ ከተማ መሆኗን ገልጸዋል። በተጨማሪም ወደ ጎንደር፣ ላሊበላና ሌሎች የቱሪስት መስህብ ስፍራዎች ለመጓዝ ለሚመጡ የውጭና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎች ዋነኛ መተላለፊያ በመሆን እያገለገለች ትገኛለች ብለዋል። ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ተርሚናል መገንባቱም ወደ ከተማዋ የሚመጡ ቱሪስቶችን ምቾትና ደህንነት በመጠበቅ የሀገራችንን ገጽታ ለመገንባት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። ሌላው በአስጎብኚነት ሥራ የተሰማሩት አቶ አበበ ያረጋል በበኩላቸው፤ ግዙፍና ዘመናዊ ተደርጎ የተገነባው ተርሚናሉ፤ ወደ አካባቢው የሚመጡ ቱሪስቶችን ያለምንም መጨናነቅና እንግልት ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላል ብለዋል። ይህም በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶችን በስፋት በመሳብ ከተማዋን ይበልጥ ለማዘመን እንደሚያግዝም አስረድተዋል። ተርሚናሉ ደረጃውን ጠብቆ መገንባቱ ለጎብኚዎች ፈጣን አገልግሎት በመስጠት የከተማዋን የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ፍሰቱን ያቀላጥፋል ያሉት ደግሞ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ጋሻው እንዳለው ናቸው። የተፈጥሮ፣ ሰው ሰራሽና ታሪካዊ ቅርሶች ባለቤት የሆነችውን የባህርዳር ከተማ በኮሪደርና በአረንጓዴ ልማት፣ በሰፋፊ የአስፋልት መንገዶችና በአዲሱ የአባይ ድልድይ ግንባታ በማጀብ ተመራጭ መዳረሻ እንድትሆን መደረጉን አመልክተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው አዲሱ ተርሚናል መንግሥት ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት ማሳያ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ በቀጣይም ዘመናዊ ሎጆችና ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎች ግንባታ ላይ ማተኮር ይገባል ብለዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 664 ሺህ 505 አዳዲስ ደንበኞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ ተደርጓል
Aug 7, 2026 164
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 664 ሺህ 505 አዳዲስ ደንበኞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው ገለጹ። የአገልግሎቱ ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው የአገልግሎቱ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅዱ ዙሪያ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ስራ አስፈጻሚው በመግለጫቸው አገልግሎቱ በበጀት ዓመቱ ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑን ጠቁመው፤ በዚህም የደንበኞቹን ቁጥርም 5 ነጥብ 88 ሚሊየን ማድረሱን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ 664 ሺህ 505 አዳዲስ ደንበኞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉንና ከዕቅድ አንጻር 83 ነጥብ 1 በመቶ መከናወኑን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ 205 የገጠር ቀበሌዎችንና መንደሮችን የኤሌክትሪክ ሀይል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም ዋና ስራ አስፈጻሚው ጨምረው አስታውቀዋል። በበጀት ዓመቱ 118 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ለደንበኞች ከቀረበ የኤሌክትሪክ ሀይል ሽያጭ መሰብሰቡንና ከዕቅድ አንጻርም 102 ነጥብ 6 በመቶ ማሳካት መቻሉን አንስተዋል። በኤሌክትሪክ ሀይል ማሰራጫ መስመር መሰረተ ልማት ዝርጋታና ጥገና ላይም ሰፊ ስራ መሰራቱን ጠቁመው በዚህም 4 ሺህ 892 ኪሎ ሜትር ያረጁ የኤሌክትሪክ ማሰራጫ መስመሮች መጠገናቸውን ገልጸዋል። ዋና ስራ አስፈጻሚው አክለውም ከ67 በመቶ በላይ አገልግሎቱ የሚጠቀምባቸው ትራንስፎርመሮች በሀገር ውስጥ የመሚመረቱ መሆናቸውን ጨምረው አስታውቀዋል። ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ለሚገጥሙ የስነምግባር ችግሮች ፈጣንና ተመጣጣኝ እርምጃዎች መውሰዱንና ይህም አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ከአንድ ሚሊየን አንድ መቶ አስራ ሶስት ሺህ አንድ አዳዲስ ደንበኞችን ለማፍራት እንዲሁም 317 የገጠር መንደሮች አዲስ ኀይል እንዲያገኙ መታቀዱን አስታውቀዋል። ከመሰረተ ልማት ማስፋፊያና ጥገና አንጻርም በአዲሱ በጀት ዓመት 12 ሺህ 549 ኪሎ ሜትር የኤሌክትሪክ መስመር እንደሚዘረጋም ገልጸዋል። የኤሌክትሪክ መቆራረጥን መቀነስ የሚያስችሉ ሰፋፊ የመሰረተ ልማት ዝርጋታ እና ጥገና ስራዎች በትኩረት ይከናወናሉ ነው ያሉት። አሁን ላይ አገልግሎቱ የሚጠቀምባቸው ከ67 በመቶ በላይ ትራንስፎርመሮች በሀገር ውስጥ እንደሚመረቱም ኢንጂነር ጌቱ ገረመው በመግለጫቸው ተናግረዋል። የኀይል መቆራረጥ ምጣኔን ለመቀነስ በትኩረት እንደሚሰራ ጠቁመው ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ለሚገጥሙ የስነምግባር ችግሮች ፈጣንና ተመጣጣኝ እርምጃዎች መውሰዱን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአርሶ አደሮችን ምርታማነት አሳድጓል
Aug 7, 2026 144
አለታ ወንዶ ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ያለፉት ዓመታት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ተግባራት ምርታማነታቸው እንዲጨምር ማድረጉን በደቡባዊ ሲዳማ ዞን የአለታ ወንዶ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ በወረዳው የዊቾ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ታፈሰ ዩጤ፤ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በየዓመቱ በግል ማሳቸውና በአካባቢው የወል መሬቶች ላይ ተከላ ሲያከናውኑ መቆየታቸውን ተናግረዋል። በዚህም በአካባቢያቸው ተራቁተው የነበሩ ቦታዎች ለምልመው ወደ አረንጓዴነት መቀየራቸውን ጠቁመዋል። በመርሃ ግብሩ የተከሏቸው የአቮካዶ፣ የማንጎ፣ የሙዝና ሌሎች ፍራፍሬዎች አሁን ላይ ለምርት በመድረሳቸው ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ገልጸዋል። የጎዋዳሞ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ካሰች ዳንሳሞ በበኩላቸው፤ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተከሏቸውን የፍራፍሬና የጥላ ችግኞች በመንከባከብ ለፍሬ እንዲበቁ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። ችግኞቹ አድገው ለቡና ማሳቸው ጥላ ከመሆናቸውም በላይ፣ ፍራፍሬዎቹ ከምግብ ፍጆታ ባለፈ የገቢ ምንጫቸውን ለማሳደግ እንዳስቻላቸው አስረድተዋል። የተሻሻሉ የአቮካዶ ዝርያዎችን በስፋት በማልማት ምርቱን ለኢንዱስትሪና ለሌሎች ገበያዎች እያቀረበ ተጠቃሚ መሆኑን ያነሳው ደግሞ የዶቤ ሰዴቃ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ወጣት ቹቹ ቢረጋ ነው። በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብርም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን የፍራፍሬ ችግኞች በመትከል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ተናግሯል። የደቡባዊ ሲዳማ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ደበበ ሻላ፤ በዞኑ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአካባቢ ሥነ-ምህዳር መጠበቁንና የአርሶ አደሩ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማደጉን ገልጸዋል። በዚም ለደንና ለምግብ የሚሆኑ ችግኞች መተከላቸውን በማንሳት፤ የአፈር ለምነትን ለመጠበቅና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ማስቻሉን ጠቅሰዋል። ለአብነትም በመርሃ ግብሩ ከተተከሉ ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኞች መካከል የቡና ምርታማነት በአማካይ ከ8 ነጥብ 5 ወደ 9 ነጥብ 2 ማደጉን ተናግረዋል። በፍራፍሬ ምርትም አርሶ አደሮች በማኅበር በመደራጀት ምርታቸውን ለይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርት ኢንዱስትሪ ፓርክና ለአዲስ አበባ ገበያ እያቀረቡ ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኙም አስረድተዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ለአሪ ዞን አርሶ አደሮች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እየሆነ ነው
Aug 7, 2026 144
ጂንካ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ለአካባቢ ጥበቃ ካለው ፋይዳ ባሻገር ተጨማሪ የገቢ ምንጭ በመሆን ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአሪ ዞን አርሶ አደሮች ገለፁ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አሪ ዞን ደቡብ አሪ ወረዳ የጎምር ቀበሌ አርሶ አደር ታደሰ ሸዋዬ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ አካባቢያቸው ተራራማና ተዳፋት በመሆኑ በተደጋጋሚ ለአፈር መሸርሸርና ለጎርፍ አደጋ ሲጋለጡ ቆይተዋል። ባለፉት ዓመታት መንግስት የአካባቢውን አርሶ አደሮች በማሳተፍ በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የአፈር መሸርሸርና ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭነታቸው እየቀነሰ መምጣቱን ገልጸዋል። የተፋሰስ ልማት በተከናወነባቸው አካባቢዎች ፍራፍሬ በማልማት በአሁኑ ወቅት ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ችግኝ በስፋት መትከል ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በአካባቢያቸው ተጨባጭ ለውጦች መታየታቸውን የገለጹት ደግሞ አርሶ አደር ገዛህኝ ገሚጋንሶ ናቸው። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር በተከናወኑ ተግባራት ያገኘነውን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በመገንዘብ ዘንድሮም ልማቱን አጠናክረን ቀጥለናል ያሉት አርሶ አደሩ፣ ልማቱ ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን ተናግረዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ሙዝ፣ አቮካዶ እና ቡና ተክለው በማልማት ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ጠቁመው፣ ይህን ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በየዓመቱ በመርሀግብሩ የሚያደርጉትን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። አካባቢው በስፋት ቡና አብቃይ በመሆኑ ለእርሻ ሥራ ምቹ ባልሆኑ አካባቢዎች ጭምር ቡና ተክለው እያለሙ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ ሌላው የቀበሌው አርሶ አደር ነሽራይ ከራልቆ ናቸው። ባለፉት ዓመታት የተከሏቸው የቡና ችግኞች ምርት መስጠት እንደጀመሩ ጠቅሰው፣ ቡና ካስገኘላቸው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ አንጻር በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብርም በስፋት መትከላቸውን ተናግረዋል። ቀደም ሲል በአካባቢው በተራቆቱ አካባቢዎች የደን ችግኞችን ብቻ የማልማት ልምድ እንደነበር ያስታወሱት ደግሞ አርሶ አደር ማርታ ማቲዮስ ናቸው። ለደን ልማት ብቻ የሚያገለግሉ ችግኞች ጥቅማቸው ውስን በመሆኑ አሁን ላይ ለምግብነት፣ ለአካባቢ ጥበቃ እና ለገቢ ምንጭነት የሚውሉ ችግኞችን ጭምር በማልማት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። የአሪ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ጉራልቅ ይዥማልቅ በበኩላቸው እንዳሉት የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብርን ተከትሎ በዞኑ እንደ ፓፓያ፣ አቮካዶ፣ ማንጎ እና አፕል ያሉ ፍራፍሬዎች በስፋት እየለሙ ይገኛሉ። ይህም የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ካለው ፋይዳ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን እያሳደገው መምጣቱን ተናግረዋል። የሀገር በቀል ዛፎች እንደ ኮሶ፣ ዋንዛ፣ ጽድ እና ዝግባ ያሉና ሥነ-ምኅዳርን ለመጠበቅ የሚያስችሉ ችግኞች በተራቆቱ ተራራማ አካባቢዎች በስፋት እየተተከሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል። የአካባቢ ጥበቃ ሥራውን ከዘመናዊ የንብ ማነብ ሥራ ጋር በማስተሳሰር አርሶ አደሮች በዘርፉ ተሰማርተው ገቢያቸውን እንዲያሳድጉ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም አቶ ጉራልቅ አስታውቀዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያረጋገጠ ነው
Aug 7, 2026 128
አርባምንጭ ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት መርሃ ግብር የአካባቢያችንን ሥነ-ምህዳር በማስተካከል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያረጋገጠ ነው ሲሉ የጋሞ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የጋጮ ባባ ወረዳ የጋጼ ቀበሌ ነዋሪዎች አርሶ አደር አልቤ አለሙ እና አርሶ አደር አቡሽ አማሮ፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ለሰብል ምርትና ለእንስሳት መኖ ልማት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል። መርሃ ግብሩ የደን ዛፎችን በመትከል ገላጣ የነበሩ ተራሮች እንዲለሙ ማደረጉን ጠቁመው፤ የአቮካዶ፣ የማንጎ እና የአፕል ፍራፍሬ ችግኞችን በማልማት የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደግ ማስቻሉን ገልጸዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የደን ሽፋን እንዲጨምር በማድረጉ በንብ ማነብ ሥራ ተሰማርተው ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ በምዕራብ አባያ ወረዳ የ«ጦይሎ» ንብ አናቢ ማኅበር ሰብሳቢ አቶ ደሴ ኡታሎ ናቸው። ማኅበሩ በ52 አባላት በ2014 ዓ.ም መመስረቱን የጠቀሱት ሰብሳቢው፤ አሁን ላይ በ19 ሄክታር ደን ውስጥ ንብ ከማነብ ባለፈ የደን ጥበቃ ሥራ እያከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የሚያመርቱትንም ማር ለአካባቢው ገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ገቢ በማግኘታቸው አባላቱ በከተማ መኖሪያ ቤት መገንባታቸውንና የሸቀጥ ሱቆችን መክፈታቸውን ገልጸዋል። የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ማጌሶ ማሾሌ በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥና ኢኮኖሚያዊ አቅምን በማሳደግ ረገድ ጉልህ ድርሻ እያበረከተ መሆኑን አስረድተዋል። መርሃ ግብሩ የዞኑን የደን ሽፋን በማሳደግ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገሩ የልማት ስራዎች እንዲተገበሩ፣ እንዲሁም የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ በማድረጉ የከርሰ ምድር ውሃ መጠንና የአፈር ለምነት እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል። በዚህም ምርትና ምርታማነት ከመጨመሩም ባሻገር አርሶ አደሩ በንብ ማነብ ሥራ ተሰማርቶ ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻሉን አክለዋል። በተጨማሪም በዞኑ የሚገኙ ተራሮች እየለሙ በመምጣታቸው በአባያና ጫሞ ሀይቆች ህልውና ላይ አደጋ እያስከተለ የነበረው የደለል አፈር በእጅጉ መቀነሱን አቶ ማጌሶ ገልጸዋል።
አገልግሎቱ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ውጤታማ ተግባራትን አከናውኗል
Aug 7, 2026 168
አዲስ አበባ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑን አስታወቀ። አገልግሎቱ የ2018 በጀት ዓመት በኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት እና የፋይናንስ አፈጻጸሙን እንዲሁም በ2019 በጀት ዓመት ዕቅዱ ዙሪያ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥቷል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው፤ አገልግሎቱ በበጀት ዓመቱ ውጤታማ ተግባራትን አከናውኗል ብለዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ በተከናወኑ በርካታ ተግባራት የደንበኞቹን ቁጥር 5 ነጥብ 88 ሚሊየን ማድረስ መቻሉን ገልጸዋል። ከደንበኞች አገልግሎት አንጻር በቅድመ ክፍያ 82 ነጥብ 6 እንዲሁም በድህረ ክፍያ 15 ነጥብ 4 በመቶ መድረሱንም አክለዋል። በበጀት ዓመቱ 664 ሺህ 505 አዳዲስ ደንበኞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን ገልጸው፤ ይህም ከዕቅዱ አንጻር 83 ነጥብ 1 በመቶ መከናወኑን ተናግረዋል። አገልግሎቱ በበጀት ዓመቱ 118 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ለደንበኞች ከቀረበ የኤሌክትሪክ ሀይል ሽያጭ መሰብሰቡን ተናግረዋል። በኤሌክትሪክ ሀይል ማሰራጫ መስመር መሰረተ ልማት ዝርጋታና ጥገና ላይም ሰፊ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል። በዚህም ያረጁ የማሰራጫ መስመሮችን ከመጠገን አንጻርም በበጀት ዓመቱ 4 ሺህ 892 ኪሎ ሜትር የኤሌክትሪክ መስመሮች ላይ የጥገና ስራ ተሰርቷል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መሪነት የአፍሪካ ኃያል ሀገር እየሆነች ነው-ታዋቂው የህንድ ሚዲያ ፈርስት ፖስት
Aug 7, 2026 209
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) መሪነት የመጪው ዘመን የአፍሪካ ኃያል ሀገር ወደመሆን እየተሸጋገረች ነው ሲል ታዋቂው የህንድ ሚዲያ ፈርስት ፖስት ዘግቧል። ፈርስት ፖስት ሚዲያ ኢትዮጵያን በተመለከተ በሠራው ትንታኔው የሰው ዘር መገኛ፣የጥንታዊ መንግስታት ምድር፣የንግድ መስመሮች እና ከፍ ያለ የአፍሪካ ታሪካዊ መሰረት ያላት ሀገር መሆኗን አውስቷል። ሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ወደ ስልጣን ከመጡ ወዲህ ከቀድሞ ገናና ታሪኳ እኩል ታላቅ የሆነ አዲስ ምዕራፍ ለመገንባት በትጋት ላይ መሆኗን አንስቷል። በጠቅላይ ሚኒስትሩ መሪነት በቀጣናው እና የአፍሪካ ኃያል ሀገር መሆን የሚያስችላትን እንዲሁም የአህጉሪቱን የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚበይንና የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት እየሠራች መሆኗንም እንዲሁ። ለረጅም ዓመታት ዓለም ኢትዮጵያን የሚያውቃት በጦርነት፣በድርቅ እና በፖለቲካዊ አለመረጋጋት እንደነበር በማስታወስ፥ዛሬ ግን ሀገሪቱ ይህንን የተዛባ ትርክት በኢነርጂ መሠረተ ልማት፣ በአቪየሽን፣ በማዕድን እና በዲጂታል ኢኮኖሚ አስደማሚ ለውጦች ለመቀየር እየሠራች ነው ብሏል። ኢትዮጵያ ፈተናዎችን ተሻግራ እንዴት በአፍሪካ ፈጣን ዕድገት ካላቸው ኢኮኖሚዎች ቀዳሚዋ ሆና ልትቀጥል ቻለች? የሚለውን ጥያቄ በማንሳትም በዝርዝር መልሶቹን ያብራራል። የዚህ ዋና ጥያቄ ዝርዝር ምላሽ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት እየተተገበሩ የሚገኙ የኢትዮጵያን የወደፊት እጣ ፈንታ የሚወስኑ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ላይ ነው ያለው ሲል አንስቷል። • የመጀመሪያው የኢነርጂ አብዮት እና ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ነው። በዚህ የኢትዮጵያ የለውጥ ጉዞ ጎልቶ የሚነሳው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሲሆን፣ ከ5 ሺህ ሜጋዋት በላይ የማመንጨት አቅም ያለው የአፍሪካ ትልቁ የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ፕሮጀክት መሆኑን ፈርስት ፖስት በዘገባው ጠቅሷል። ሕዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ መሻቶች መሰረት፣የኤሌክትሪክ ኃይል፣ የውጭ ምንዛሬ እና የቀጣናዊ ተጽዕኖ መፍጠሪያ አቅም መሆኑንም አብራርቷል። የሕዳሴ ግድብ ልዩ የሚያደርገው የኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝብ ከዓለም ባንክ ወይም ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም አንድ ሳንቲም ሳይበደር በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደም፣ ላብና ገንዘብ የተገነባ አፍሪካውያን በራሳቸው ህልማቸውን ማሳካት እንደሚችሉ ያሳየነው ብሏል። ለኢትዮጵያውያን ግድቡ ከኮንክሪት እና ከተርባይን በላይ ትርጉም አለው ያለው ይህ የፈርስት ፖስት ዘገባ፥ እጅግ የላቀ እራስን የመቻል እና የኢኮኖሚ ነፃነት ማሳያ ሐውልት መሆኑንም ተንትኗል። ኢትዮጵያ ታዳሽ ኃይልን ለኬንያ፣ ለጂቡቲ እና ለሱዳን በመሸጥ ኤሌክትሪክን ወደ ከፍተኛ ገቢ ማመንጫነት እየቀየረች ከመሆኑም በላይ የመላው ምስራቅ አፍሪካ ቀጣናዊ የትስስር ማዕከል ሆናለች ነው ያለው። • የኢትዮጵያ የዕድገት ምሰሶ አቪዬሽን እና ቀጣናዊ ትስስር ኢነርጂ ብቻውን ኢኮኖሚያዊ አቅምን አይገነባም፤ ይልቁንም ኢነርጂ ኢንዱስትሪን ያነቃቃል፣ ትስስር ዓለም አቀፍ ንግድን ይመግባል ያለው ፈርስት ፖስት፥የአፍሪካ ግዙፉ አየር መንገድ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አሁን ለላቀ የዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ጉዞ መጀመሩን አንስቷል። በ12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ግንባታው እየተፋጠነ የሚገኘው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በየዓመቱ እስከ 110 ሚሊዮን ተጓዦችን እና ወደ 4 ሚሊዮን ቶን የሚጠጋ የዕቃ ጭነት ማስተናገድ አቅም አለው። ሙሉ በሙሉ ግንባታው ሲጠናቀቅም በዓለም አቀፍ ደረጃ ከታላላቅ የአቪዬሽን ማዕከላት አንዱ ይሆናል ብሏል። ይህ ፕሮጀክት የአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የዲፕሎማሲ መናኸሪያ የሆነችውን አዲስ አበባንና አፍሪካን፣ከሌሎች የዓለም ክፍሎች የሚያስተሳስር ዋና የመተላለፊያ ማዕከል እንደሚሆንም ተገልጿል። ስለዚህ አዲሱ የቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ ለንግድ፣ ለኢንቨስትመንት እና ለቱሪዝም፣ ለዓለም የዲፕሎሲ ትብብር ጉልህ ሚና እንዲያበረክት ታስቦ እየተገነባ ነው ብሏል። • የማዕድን ኢንቨስትመንትና በምግብ ራስን መቻል በሌላ በኩል ከኢትዮጵያ መሬት በታች ላለው የማዕድን ሀብቷ ትኩረት በመስጠት የልማት አብዮት እያካሄደች ስለመሆኑም ተንትኗል። ሀገሪቱ የወርቅና ሌሎች ማዕድናት ማውጫ ሜጋ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት አዳዲስ የውጭ ምንዛሬ ምንጮችን እያፈራች የማዕድን ኢንዱስትሪዋን እያሳደገች ነው። ወርቅ በፍጥነት ከኢትዮጵያ ቀዳሚ የወጪ ንግድ ምርቶች አንዱ በመሆን ለረጅም ጊዜ በግብርና ላይ ብቻ ጥገኛ ሆኖ የቆየውን ኢኮኖሚ ወደ ብዝኃ ዘርፍ እያሸጋገረ ይገኛል። በሌላ በኩል በምግብ ራስን ከመቻል ውጭ የትኛውም ኢኮኖሚያዊ ለውጥ የተሟላ ሊሆን አይችልም ያለው የፈረስት ፖስት ዘገባ፥ ግብርና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት መሆኑን ጠቅሷል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሚመራው መንግሥት ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን እንድትችል በጀመረው የለውጥ ጉዞ አስደማሚ ውጤት እያመጣ ነው ብሏል። ከዚሁ ጋር በተያያዘም ከጉባ ብስራቶች አንዱ የሆነውና በሶማሌ ክልል እየተገነባ የሚገኘው የማዳበሪያ ፋብሪካ ፕሮጀክት በየዓመቱ 3 ሚሊዮን ቶን የሚጠጋ ዩሪያ ማዳበሪያ ማምረት የሚችል ነው። ይህም ከውጭ የሚገባውን ማዳበሪያ ጥገኝነት በመቀነስ የኢትዮጵያን የግብርና ምርታማነት ለማሳደግ እንደሚያስችል አብራርቷል። "የምግብ ዋስትና የእኛ ስትራቴጂካዊ ጣልቃ ገብነት ነው።ያንን ግብ እውን ለማድረግ ግብአቶች ላይ መስራት አለብን።በግብአት ላይ መስራት ካልተቻለ የምግብ ዋስትናን እውን ለማድረግ መንገድ የለውም" የሚለውን የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ በማካተት ዘገባው ሰፊ ሽፋን ሰጥቷል። ዲጂታላይዜሽን እና የኢንቨትመንትና የገበያ ማሻሻያዎች በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለው ለውጥ ወደ ዲጂታልም እየተሸጋገረ ነው።ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እንደተናገሩት የ5 ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ስልጠና ከዕቅዱ ቀድም ከመሳካቱም በላይ በርካታ ወጣቶች የዲጂታል እውቀት ባለቤት አድርጓል። በተመሳሳይ የዲጂታል ትስስር እየሰፋ ሲሆን የ4ጂ እና 5ጂ አገልግሎቶች በበርካታ ከተሞች ተደራሽ ሆኗል። ኢትዮጵያ ለበርካታ አስርት ዓመታት ተዘግተው የቆዩ እንደ ቴሌኮሙኒኬሽን፣ ባንክ እና የካፒታል ገበያዎች ያሉ ዘርፎችን ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት ማድረጓንም አድንቋል። የካፒታል ገበያን መጀመሯም የግል ካፒታል ልውውጥን በማጎልበት ለኢኮኖሚ ዕድገት ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ተንትኗል። እነዚህ ማሻሻያዎች በአጠቃላይ በመንግስት ቁጥጥር ስር ከነበረው የኢኮኖሚ ወደ ግል ዘርፍ ኢንቨስትመንት እያደገ የሚሄድ ኢኮኖሚ መሰረታዊ ለውጥን እየተገነባ መሆኑን ያሳያሉ ነው ያለው። ኢትዮጵያ ካላት የጂኦ ፖለቲካ ስትራቴጂካዊ አቀማመጥ አኳያ እድልና ፈተናዎች ከፊቷ መሆናቸውን በማንሳት፥ አዲሱን የዓለም አቀፍ የትብብር ጥምረት ብሪክስ አባል መሆኗን አውስቷል። ከቻይና፣ ከመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት፣ ከምዕራባውያን አጋሮችና ከአፍሪካ ኢንቨስተሮች ኢንቨስትመንትን እየሳበች እንደምትገኝም እንዲሁ። ኢትዮጵያ ጎራ ሳትለይ ከሁሉም የዓለም ሀገራት ጋር ትብብሯን እያጠናከረች ነው ብሏል። ዓለም ኢትዮጵያን የምታስታውሰው በጦርነት ቢሆንም፥ኢትዮጵያ ዓለም በአዲሱ የለውጥና የስኬት ጉዞዋ እንዲያስታውሳት እየሠራች ነው። ለዚህም በመላው ሀገሪቱ በሁሉም ዘርፍ ግዙፍ የኢኮኖሚ ሽግግር እየተካሄደ ሲሆን፥ ይህ የኢትዮጵያ ጉዞ ለቀጣዮቹ ዓመታት የቀጣናውንና የአፍሪካን ኢኮኖሚያዊና አጠቃላይ ገጽታ በአዲስ መልኩ የሚቀርጽ ነው ሲል ፈርስት ፖስት ዘገባውን አብራርቷል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት 67 ቢሊዮን ብር በጀት አፀደቀ
Aug 7, 2026 203
ወልቂጤ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት ለ2019 በጀት ዓመት 67 ቢሊዮን ብር በጀት አፀደቀ። ምክር ቤቱ በጀቱን ዛሬ ያጸደቀው በወልቂጤ ከተማ እያካሄደ ባለው 6ኛ ዙር፣ 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን ስድስተኛ መደበኛ ጉባኤው ነው፡፡ በምክር ቤቱ የፕላን፣ መሰረተ ልማትና የመንግስት ሃብት ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ታመነ ገብሬ የክልሉ መንግስት የ2019 ረቂቅ በጀት 67 ቢሊዮን ብር መሆኑን በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ በጀቱ በክልሉ ከውስጥ ገቢ በሚሰበሰብ እና ከፌደራል መንግስት በሚመደብ በጀት የሚሸፈን መሆኑንም ገልጸዋል። የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ ዘይቱና ኢብራሒም በበኩላቸው በጀቱ የክልሉን የልማት ፍላጎት ለማሳደግ ታሳቢ ተደርጎ የተመደበ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በተለይ ተጀምረው ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ እንዲሁም የሕዝብን የመሰረተ ልማት ጥያቄ መመለስ ለሚችሉ የልማት ሥራዎች ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። በተጨማሪም በጀቱ በገጠር እና በከተማ ለአዳዲስ የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለመስኖ ልማት እንዲሁም የተጀመሩ እና ቀጣይ በአዲስ ለሚሰሩ ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ እንደሚውል አመልክተዋል። ምክር ቤቱ በቀረበው የክልሉ የ2019 ረቂቅ በጀት ላይ ከተወያየ በኋላ አጽድቋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን ከ184 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኩታ-ገጠም አሰራር በበቆሎ ሰብል እየለማ ነው
Aug 7, 2026 176
አምቦ ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን በዘንድሮው የመኸር ወቅት ከ184 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኩታ-ገጠም አሰራር በበቆሎ ሰብል እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በኦሮሚያ ክልል የምዕራብ ሸዋ ዞን፣ ለእርሻ ስራ ተስማሚ በሆነው አየር ንብረቱ እና ለም አፈር ምክንያት ከሀገሪቱ ዋነኛ የሰብል አምራች አካባቢዎች አንዱ ነው። በዞኑ ከሚመረቱት ዋና ዋና ሰብሎች መካከል በቆሎ የመጀመሪያውን ደረጃ የሚይዝ ሲሆን፣ ለአካባቢው አባወራዎች የምግብ ዋስትና እና ገቢ ማግኛ ዋነኛ መሰረት ነው። በክልሉ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተዘረጋው የኩታ-ገጠም የእርሻ አሰራር አነስተኛ አራሾች መሬታቸውን አስተባብረው በጋራ እንዲያርሱ የሚያስችል ስልት ነው። ይህ አሰራርም የቴክኖሎጂ እና ግብአት አጠቃቀምን ለማሳደግ፣ ምርታማነትን ለመጨመርና የገበያ ትስስር ለመፍጠር ጉልህ ድርሻ አለው። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፍ አቶ ተረፈ አራርሳ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በ2108/19 የመኸር ወቅት 219 ሺህ 767 ሄክታር መሬት በበቆሎ ሰብል ለመሸፈን ታቅዶ ከእቅድ በላይ 226 ሺህ 788 ሄክታር ማልማት ተችሏል። ከዚህ ውስጥ ከ184 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በኩታ-ገጠም(ክላስተር ) እየለማ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በተለይም እንደ ሀገር ድህነትን ለማስወገድና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተነደፉ አቅጣጫዎችን በመከተል፣ በክልሉም በአዳዲስ እሳቤዎች ላይ የተመሰረቱ ሀሳቦችን ወደ ተግባር ለመለወጥ የተቀናጀ የህዝብና የአመራር ርብርብ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በዚህ ረገድ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ለአርሶ አደሩ በማስተዋወቅና በማላመድ፣ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር ለገበያና ለኢንዱስትሪ የሚሆኑ ግብዓቶችን ለማቅረብ ልዩ ትኩረት መሰጠቱን አውስተዋል። በምርት ዘመኑ በዞኑ በበቆሎ ሰብል ከተሸፈነው አጠቃላይ መሬት 13 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስረድተዋል። በዞኑ የኖኖ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ወንዳፍራሽ ሉሌሳ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው የምርት ዘመን በወረዳው 54 ሺህ 433 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ተሸፍኗል። ከዚህ ውስጥ 26 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በበቆሎ ሰብል እየለማ መሆኑን ጠቁመዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የወረዳው አርሶ አደሮች በበኩላቸው እንደተናገሩት፣ ከዚህ ቀደም ከአንድ ሄክታር መሬት የሚያገኙት ምርት ከ12 ኩንታል የሚበልጥ አልነበረም። ዘንድሮ ግን በኩታ-ገጠም (ክላስተር) ካለሙት የበቆሎ ሰብል በሄክታር ከእጥፍ በላይ ምርት ለማግኘት አቅደው አስፈላጊውን እንክብካቤ እያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል አቶ ሸለማ ወርቁ በኩታ-ገጠም አሰራር ዘር መዝራታቸውን ጠቅሰው፣ ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀማቸው የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል። ሌላኛው የወረዳው አርሶ አደር ገረሙ ኢዶሳ በበኩላቸው፣ በየዓመቱ በባለሙያ ምክር በመታገዝ በቆሎ በስፋት እንደሚያመርቱና ዘንድሮም የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል።
የባህር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲሱ ተርሚናል ሰፊ የኢኮኖሚ ዕድል ይፈጥራል
Aug 6, 2026 793
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ) ፦የባህር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲሱ ተርሚናል የጎብኚዎችን ፍሰት በማሳደግ በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች ሰፊ የኢኮኖሚ ዕድል ይፈጥራል ሲሉ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። የባህር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲሱ ተርሚናል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ተመርቋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በዚሁ ወቅት፣ የባህር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲሱ ተርሚናል የጎብኚዎችን ፍሰት በማሳደግ በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች ሰፊ የኢኮኖሚ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በክልሉ በርካታ የልማት ስራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን፣ ከተሞች ለነዋሪዎቻቸው ምቹና ዓለም ዓቀፍ ተወዳዳሪነታቸውን ከፍ ለማድረግ በጎንደር፣ በባህር ዳር፣ በወልዲያ፣ በደሴና በሌሎች ከተሞችም እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የክልሉን ሁለንተናዊ እድገት የሚያሳልጡና የቱሪዝም ልማቱን የሚያፋጥኑ እንዲሁም የህዝብ ለህዝብ ትስስርን የሚያጠናክሩ አውሮፕላን ማረፊያዎችን ጨምሮ ሌሎች በርካታ ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ባህር ዳር በጣና ሐይቅ፣ በባህላዊ ቅርሶችና በተፈጥሯዊ መስህቦች የበለጸገች በመሆኗ፣ የአየር ትራንስፖርት አቅሟ መጠናከር የጎብኚዎችን ፍሰት በማሳደግ በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች ሰፊ የኢኮኖሚ ዕድል ይፈጥራል ነው ያሉት። በክልሉ በፌዴራል መንግስት ድጋፍ የቱሪዝም፣ የከተማ ልማትና የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች በስፋት እየተከናወኑ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ክልሉን ተመራጭ የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ እንደ ጎርጎራ ሪዞርት እና ጣና ሎጎ ሀይቅ ሪዞርት ያሉ ታላላቅ የቱሪስት የመዳረሻ ልማቶች ተገንብተው ለአገልግሎት መብቃታቸውን አስታውሰዋል። የባህር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲሱ ተርሚናልም እነዚህን የልማት ሥራዎች በመደገፍ ለከተማዋ የቱሪዝም፣ የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የኮንፍረንስ ቱሪዝም እድገት አዲስ አቅም በመፍጠር የክልሉን ተወዳዳሪነት ያጠናክራል ብለዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው በበኩላቸው፣ የባህር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲሱ ተርሚናል በዘመናዊ የአየር ማረፊያ ደረጃዎች መሠረት መገንባቱን አስታውቀዋል። የተሻለ የተሳፋሪ አገልግሎት በመስጠትም የከተማዋን የአየር ትራንስፖርት ተደራሽነት እንደሚያጠናክር ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሀገሪቱ የአየር ትራንስፖርት መሠረተ ልማትን ለማስፋፋት እያከናወነ ያለው ተግባር ከተሞችን ከኢኮኖሚ፣ ከንግድና ከቱሪዝም ዕድሎች ጋር በተሻለ ለማገናኘት ያለመ ነው ብለዋል። አዲሱ ተርሚናል ባህር ዳርን በአየር ትራንስፖርት የበለጠ ተደራሽ በማድረግ የቱሪዝም እድገትን፣ የንግድ እንቅስቃሴን፣ የኢንቨስትመንት መስፋፋትንና የሥራ ዕድል ፈጠራን በማጠናከር ለከተማዋና ለአካባቢው ኢኮኖሚ ጉልህ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት በመርሃ ግብሩ ተመላክቷል።
በባሕር ዳር ከተማ የተከናወኑ አበረታች የልማት እንቅስቃሴዎች የብልፅግና አቅጣጫዎችን በግልጽ ያመላከቱ ናቸው
Aug 6, 2026 781
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ) ፦በባሕር ዳር ከተማ የተከናወኑ አበረታች የልማት እንቅስቃሴዎች የብልፅግና አቅጣጫዎችን በግልጽ ያመላከቱ መሆናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በባህር ዳር ከተማ የደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተርሚናል ዛሬ መርቀው ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በባህር ዳር እና አካባቢዋ መልካም የልማት ጅምሮች መኖራቸውን መናገር ይቻላል ብለዋል፡፡ በቅርብ ጊዜ ውስጥ የጎርጎራ ሪዞርት እና በባህር ዳር ከተማ ውስጥ የሚገኘው "ፈለገ ጊዮን" ተገንብተው ለአገልግሎት በቅተዋል ብለዋል ። ሁለቱን ታሪካዊና የቱሪስት መስህብ ስፍራዎች ማገናኘት የሚችሉ በርካታ መርከቦች፤ በተለይም በኢትዮጵያ ትልቁ የሆነው "ጣና ነሽ" የተሰኘችው መርከብ ወደ አካባቢው እንድትመጣ መደረጉን አመልክተዋል። ባህር ዳር በቱሪዝም ዘርፍ ለሀገሪቷ ማበርከት የምትችለው በርካታ የታሪክና የተፈጥሮ ሀብት እንዳላት አመልክተው፤ ይህ ሁሉ ጥረትና ኢንቨስትመንት ሊደረግ መቻሉን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል፡፡ በባሕር ዳር ከተማ ከመንግሥት ባሻገር በግል ባለሀብቶች ተሳትፎ በርካታ የቱሪዝም ዘርፍ ልማቶች ተጠናቅቀው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውንም ገልጸው፤ ሌሎችም በቅርቡ የሚጠናቀቁ መሆኑንም አብራርተዋል። እነዚህ አበረታች ሥራዎች የከተማዋን የቱሪዝም ዘርፍ ከማነቃቃታቸውም በላይ ከሀገራዊ ለውጡ በኋላ በከተማዋ የተከናወኑ የልማት አቅጣጫዎችን የሚያመላክቱ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከለውጥ በኋላ ባህር ዳር ከቱሪዝም በተጨማሪ በኢንዱስትሪ ከፍተኛ የእድገት አቅም እንዳላት አመልክተው፤ ይህንንም ወደ ተጨባጭ ኢኮኖሚ ለመቀየር ትልቅ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ተገንብቶ ወደ ሥራ መግባቱን ገልጸዋል፡፡ በሀገር እና በአህጉር ደረጃ ግዙፍ የሆነ ድልድይ የተገነባ መሆኑን ጠቁመው፤ ከተማዋን የበለጠ ውብና የኢኮኖሚ ማዕከል የሚያደርግ የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ ግንባታው ሲጠናቀቅ በርካታ የሀገር ውስጥና የውጭ እንግዶችን የሚያስተናግድ ስታዲየም እየተገነባ መሆኑን አመልክተዋል። ከቦሌ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት ቀጥሎ በኢትዮጵያ ሁለተኛው ትልቅ ተርሚናል በባህር ዳር መገንባቱ ለከተማዋ፣ ለክልሉ እና ለሀገሪቷ ትልቅ እሴት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በከተማዋ የተገነባው ዘመናዊ ኤርፖርት ተርሚናል ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ የልማት አቅሟ በጥረትና በትጋት ልቆ እንዲታይ ማድረግ እንደሚቻል የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህንንም ወደ ተጨባጭ ውጤት ለመቀየር የህብረተሰቡ ትብብር ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተከናወነውን ሪፎርም አድንቀው፤ ፕሬዝዳንቱ ከቢሯቸው ሆነው የክልሉን ችሎቶች በቨርቹዋል ለመከታተልና ቅሬታ ለማዳመጥ የሚያስችል አሰራር በመዘርጋታቸው ምስጋና አቅርበዋል፡፡
በሐረሪ ክልል 47 አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ ገብተዋል
Aug 6, 2026 720
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በ2018 በጀት ዓመት 47 አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ መግባታቸውን የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ ወደ ስራ የገቡ ኢንዱስትሪዎች ለዜጎች የስራ እድል እየፈጠሩ መሆናቸውም ተገልጿል። የቢሮው ምክትል ሃላፊ ሃምዲ ሰለሃዲን እንደገለጹት በክልሉ በተለይም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪውን የማምረት አቅም ከማጎልበት ባለፈ በዘርፉ መነቃቃት እንዲፈጥር እያስቻለ ነው። ወደ ስራ የገቡት ኢንዱስትሪዎች ወደ ውጪ የሚላኩ ምርቶችን በማጎልበትና ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጪ ምንዛሬን እያስቀሩና ለኢኮኖሚው ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያበረከቱ እንደሚገኙም ገልጸዋል። በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት 47 መካከለኛ እና አነስተኛ አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ እንደገቡ ገልጸው፣ ተጨማሪ 16 አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ደግሞ የግንባታ ሥራቸውን አጠናቀው ወደ ማሽነሪ ተከላ ሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። ሥራ የጀመሩ ኢንዱስትሪዎችም ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጪ ምንዛሬን ከማስቀረት አንጻር ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያበረከቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል። አምራች ኢንዱስትሪዎቹ ከሃይል አቅርቦትና ከመሰረተ ልማት ጋር በተያያዘ ያሉባቸውን ችግሮች ለመፍታት መሰራቱን ገልጸው ዘንድሮ በኢንዱስትሪ ዘርፉ ብቻ 3 ሺህ 935 ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚ የሥራ እድል ተፈጥሯል ብለዋል። በቀጣይም የኢንዱስትሪ ዘርፍ የማጎልበት ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ ሲሉም አቶ ሀምዲ ገልጸዋል። በፋብሪካዎቹ የስራ እድል የተፈጠረላቸው ወጣቶችም እራሳችውንና ቤተሰባቸውን ከመደጎም ባለፈ ልምድ እየቀሰሙና በትርፍ ጊዜያቸውም የኮሌጅ ትምህርት እንዲከታተሉ እድል እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል። በሐረሪ ክልል 196 ከፍተኛ፣ መካከለኛና አነስተኛ አምራች ኢንዳስትሪዎች በማምረት ስራ ላይ እንደሚገኙም ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
ፓርኩን በማልማትና በመጠበቅ ዘላቂ የገቢ ምንጭ ለማድረግ ቅንጅታዊ ሥራን ማጠናከር ይገባል
Aug 6, 2026 476
ሮቤ ፤ ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ) ፦የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን በማልማትና በመጠበቅ ዘላቂ የገቢ ምንጭ ለማድረግ በቅንጅት መሥራት እንደሚገባ የኢትዮጵያ ዱር እንስሳትና ጥበቃ ባለሥልጣን አስታወቀ። በዓለም አቀፍ ቅርስነት የተመዘገበው የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ከ2019 አስከ 2029 ዓ.ም የሚተዳደርብት የአስር ዓመት ማኔጅመንት ፕላን ላይ የሚመክር አውደ ጥናት በባሌ ሮቤ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ ላይ የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ ኩመራ ዋቅጅራ እንደገለጹት፤ ልቅ ግጦሽ፣ የደን ጭፍጨፋና ሕገወጥ ሰፈራ የፓርኮችን ህልውና ሲፈታተኑ ከነበሩት ችግሮች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው። ባለፉት ዓመታት በብሔራዊ ፓርኮችና ጥብቅ አካባቢዎች በቅንጅት በተሰሩ ሥራዎች ፓርኮችን የሚፈታተኑ ተግዳሮቶች እየቀነሱ መጥተዋል። በተለይ የፌደራል፣ የክልልና የፓርኮች አካባቢ አስተዳደሮች ከማኅበረሰቡ ጋር በመሆን ባደረጉት የተቀናጀ ጥረት በፓርኮች ላይ ሲደርሱ የነበሩ እነዚህ ችግሮች መቀነሳቸውን ነው ያስረዱት። ባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን በማልማትና በመጠበቅ ዘላቂ የገቢ ምንጭ ለማድረግ በቅንጅት መሥራት እንደሚገባም ዳይሬክተሩ አቶ ኩመራ አስገንዝበዋል። ፓርኩን በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት ለማስመዝገብ የዞኑ አመራሮችና ነዋሪዎች ድርሻ ከፍተኛና ታሪካዊ እንደነበርም አስታውሰዋል። ብሔራዊ ፓርኩ በዓለም ቅርስነት ከተመዘገበ በኋላም በውስጡ ሰፍረው ለነበሩ ነዋሪዎች አስፈላጊው ድጋፍ ተደርጎ ወደ ሌላ አካባቢ እንዲዘዋወሩ መደረጉ ትልቅ ውሳኔ የሚጠይቅ በመሆኑ የዞኑን አስተዳደር አመስግነዋል። ዋና ዳይሬክተሩ እንዳሉት ፓርኩ በቀጣይ የሚተዳደርበት የአስር ዓመት ማኔጅመንት ፕላን በዘርፉ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ በጎ ተግባራትን በማስቀጠል ፓርኩን የተሻለ ደረጃ ላይ የማድረስ ግብ አለው። የባሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሃኪም አልይ በበኩላቸው እንዳሉት፣ አስተዳደሩ ብሔራዊ ፓርኩንና በውስጡ ያለውን ብዝኃ ህይወት በአግባቡ እንዲጠበቅ በትኩረት እየሰራ ነው። የፕላኑ ዋና ዓላማም ፓርኩን በመጠበቅና በማልማት የአካባቢውን ማኅበረሰብ ዘላቂ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ መሆኑን ተናግረዋል። አስተዳደሩ ፓርኩን ለማልማትና ለመጠበቅ በየደረጃው ከሚገኙ ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር መስራቱን በቀጣይም አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ለውይይት የቀረበው የአስር ዓመት ማኔጅመንት ፕላን ሁሉንም ባለድርሻ አካላት በማሳተፍ የተዘጋጀ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ኃላፊ አቶ ሻሚል ከድር ናቸው። ፕላኑ ተግዳሮቶችን ለይቶ በመፍታት ፓርኩን ለመጠበቅና ለዘላቂ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ ለማዋል እንደሚያስችል ተናግረዋል። ፕላኑም በሚቀጥሉት አሥር ዓመታት በቱሪዝም ልማት ዘርፍ፣ በመሰረተ ልማትና በስነ-ምህዳር ጥበቃና አመራር ረገድ ለመድረስ የታቀደውን ዝርዝር ተግባር ማካተቱን አቶ ሻሚል ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም (ዩኔስኮ) ካስመዘገበቻቸው ዓለም አቀፍ ቅርሶች መካከል አንዱ የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ነው። ፓርኩ የደጋ አጋዘንና ቀይ ቀበሮን ጨምሮ የበርካታ ዱር እንስሳት፣ አዕዋፋትና ዕፅዋት መኖሪያም እንደሆነ ይታወቃል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያን ለማደናቀፍ በሚንቀሳቀሱ አካላት ላይ መንግሥት የማያዳግም እርምጃ መውሰዱን አጠናክሮ ይቀጥላል
Aug 6, 2026 290
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ) ፦በኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያን ለማደናቀፍ በሚንቀሳቀሱና የሀገር ሀብት በሚመዘብሩ አካላት ላይ መንግሥት የማያዳግም እርምጃ መውሰዱን አጠናክሮ እንደሚቀጥል የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር እናትዓለም መለሰ ገለጹ። የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር እናትዓለም መለሰ በሙስና፣ በብልሹ አሰራር እና በህገ-ወጥ እንቅስቃሴዎች ላይ የተወሰዱ እርምጃዎችን አስመለክተው ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ መንግሥት ከህዝብ የቀረቡለትን ጥቆማዎች እና አቤቱታዎች መነሻ በማድረግ በልዩ ልዩ የአገልግሎት መስጫ ማዕቀፎች እና የኢኮኖሚ ዘርፎች ላይ ያካሄዳቸውን ጥልቅ ፍተሻዎች፣ የምርመራ ውጤቶች እና የተወሰዱ የህግ ተጠያቂነት እርምጃዎችን አስመልክተው ነው ዝርዝር መግለጫ የሰጡት፡፡ በመግለጫቸው እንደጠቆሙት፤ የመደመር መንግሥት ያልተገባ ሀብት እና ጥቅም የመፈለግ አዝማሚያዎችን የሀገር እድገት አደጋ አድርጎ በመውሰድ ገና ከጠዋቱ ቀይ መስመር በማስመር ህጋዊ እና ተቋማዊ ሪፎርሞችን ሲያካሂድ ቆይቷል ብለዋል። ይህ መረጃ በብሔራዊ መረጃ እና ደህንነት አገልግሎት፣ በፌደራል ፖሊስ እና በኢፌዴሪ ፍትህ ሚኒስቴር በጋራ የተቀናጀ ስልታዊ ጥናት፣ ክትትል እና ህጋዊ ፍተሻ የተገኘ ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። እነዚህ እርምጃዎች ኢትዮጵያ እያካሄደች ያለችውን የብዙሃን ዘርፍ ማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም እና የህዝቦቿን ህይወት የመቀየር ሂደት ከሚያጋጥሙ እንቅፋቶች ለመጠበቅ ያለሙ ናቸው ብለዋል። በዚህም በትልቁ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ላይ አደጋ ለመፍጠር፣ ምርቶችን በመጋዘን በመሸሸግ እና በመደበቅ የምርት እጥረት እንዲከሰት ያደረጉ፣ በኮንትሮባንድ ንግድ የተሰማሩ እና የተጋነነ የዋጋ ጭማሪ በመፍጠር በህብረተሰቡ ላይ የኑሮ ጫና እና ምሬት እንዲፈጠር ያደረጉ አካላት ላይ ሰፊ ኦፕሬሽን መካሄዱን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ከ7 ሺህ በላይ የሚሆኑ የንግድ ተቋማት፣ ሱቆች እና መጋዘኖች በህግ እርምጃ ተወስዶባቸዋል፤ እንዲዘጉም ተደርገዋል ብለዋል። ህገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን በመቀመር፣ በጥቁር ገበያ እና በህገ-ወጥ ሐዋላ በመሰማራት፣ እንዲሁም ነጋዴዎች ከባንክ ማግኘት የሚገባቸውን የውጭ ምንዛሬ እንዳያገኙ እንቅፋት በሆኑ አካላት ላይ እርምጃ መወሰዱን ገልጸዋል፡፡ የውጭ ምንዛሬን በስውር በማንቀሳቀስ እና ጥቁር ገበያን በማስፋፋት የተጠረጠሩ 169 ግለሰቦች እና የንግድ ተቋማት በህግ አግባብ ተጠያቂ ሆነዋል ብለዋል። በተጨማሪም በፋይናንስ ተቋማት፣ ኤቲኤም ማሽኖች እና በግለሰቦች አካውንት ላይ የሳይበር ማጭበርበር የፈጸሙ እና ያለፈቃድ የክሪፕቶ ከረንሲ መተግበሪያዎችን ሲጠቀሙ የነበሩ ተቋማት በህግ እንዲጠየቁ ተደርጓል ብለዋል። በሌላ በኩል፣ ያለፈቃድ በመንቀሳቀስ በማህበረሰቡ እና በወጣቶች ላይ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ቀውስ ያመጡ፣ ግብር የሚሸሹ 36 ህገ-ወጥ የቤቲንግ ድርጅቶች እና በበየነ መረብ የሚሰሩ ተቋማት እንዲዘጉ እና በህግ እንዲጠየቁ ተደርጓል ብለዋል። ከሀገሪቱ አምስት የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ በሆነው የማዕድን ዘርፍ በተለይም በወርቅ ምርት ላይ የሚከናወነውን የኮንትሮባንድ ዝውውር እና ድለላ ለማስቆም በተደረገ ተደራጅቶ የመስራት ምርመራ፣ ምርቱን ወደ ብሔራዊ ባንክ ከማስገባት ይልቅ ለማሸሽ የሞከሩ አምራቾች፣ አዘዋዋሪዎች እና ደላሎችን ጨምሮ 138 ግለሰቦች በህግ ቁጥጥር ስር ውለዋል ብለዋል። መንግሥት ህዝቡን ከጫና ለመጠበቅ ከፍተኛ በጀት በሚመድብበት የነዳጅ አቅርቦት ላይ የሎጂስቲክስ እና የስርጭት አሻጥር በመፍጠር፣ ነዳጅን ወደ ጎረቤት ሀገራት በማሸሽ፣ መጋዘን ውስጥ በመደበቅ እና ኮታን ለግል ጥቅም በማዋል የቀውስ አዝማሚያ የፈጠሩ አካላት ተለይተዋል። በዚህ የተደራጀ ጥቅም ትስስር ውስጥ የተሳተፉ የመንግሥት አካላት፣ ነጋዴዎች እና የሎጂስቲክስ ባለሙያዎች በህግ ቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን፣ ስርዓቱን ከሙስና የጸዳ ለማድረግ ጥብቅ መመሪያ ወጥቷል ብለዋል። አርሶ አደሩ ግብአቱን በወቅቱ እንዳያገኝ ያደረጉ፣ የኮንትራክተሮች እና የደላሎች አሻጥር ያለበት የተጋነነ ዋጋ ያለው ግዢ እንዲፈጸም ያደረጉ እና ግዢው እንዲጓተት ያደረጉ አካላት በጥልቀት ተመርምረዋል ብለዋል። በዚህም ድርጊት የተሳተፉ ከፍተኛ አመራሮች፣ ደላሎች እና ግለሰቦች በህግ አግባብ ተጠያቂ ሆነዋል። በተቋሙ የፕሮጀክት ስራዎች ላይ የተጋነነ ዋጋ በመጠየቅ፣ የኃይል መሰረተ ልማት ግንባታዎች እንዲጓተቱ በመመሣጠር ሀገር ላይ የኢኮኖሚ ጫና ለማሳደር የሞከሩ የመንግሥት ኃላፊዎች፣ የፕሮጀክት አስተባባሪዎች፣ ተባባሪ ኮንትራክተሮች እና ነጋዴዎች በጥናት ተደርሶባቸው ተጠያቂ እንዲሆኑ ተደርጓል ብለዋል። በስራ እና ክህሎት ሚኒስቴር ማዕቀፍ የሚከናወነውን ዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ እና የዜጎችን ደህንነት የሚያዛቡ፣ ህጋዊ ውል ከሌላቸው ሀገራት ጋር አየር በአየር እና በህገ-ወጥ ኤጀንሲዎች ውል በማስመሰል ሲላኩ የነበሩ፣ 8 ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች፣ ኤጀንሲዎች እና ደላሎች በህግ ተጠያቂ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም በሊቢያ፣ በጅቡቲ እና በሞያሌ ድንበሮች በኩል በህገ-ወጥ መንገድ ዜጎችን ሲያሸሹ በነበሩ ደላሎች ላይ የተጀመረው ምርመራ ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል። በጉምሩክ እና ገቢዎች ዘርፍ የተዛባ የግብር ግምት በማድረግ፣ የታክስ ስወራ እንዲኖር በር በመክፈት፣ የገቢ እቃዎችን ዋጋ በመቀነስ እና ሀገሪቱ በቢሊዮኖች የሚቆጠር የመንግሥት ገቢ እንድታጣ ከነጋዴዎች ጋር በመመሣጠር የሙስና መረብ የዘረጉ ባለሙያዎች እና አመራሮች ላይ የማጥራት እና የህግ እርምጃ ተወስዷል ብለዋል። መንግሥት አገልግሎቶችን በዲጂታል በማስደገፍ፣ አሰራሮችን በማዘመን እና ተጠያቂነትን በማስፈን የጀመረውን የተቀናጀ ፀረ-ሙስና ትግል አጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቅሰዋል። ህዝቡም ጥቆማዎችን በመስጠት እና ከጸጥታና ፍትህ ተቋማት ጎን በመቆም የሚያደርገውን ትብብር አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው በባሕር ዳር ከተማ ቁልፍ የልማት ቦታዎችን ጎበኙ
Aug 6, 2026 217
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ) ፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው ከከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ጋር በመሆን በባሕር ዳር ከተማ ቁልፍ የልማት ቦታዎችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል። በጉብኝታቸውም ከተማዋ ያላትን እምቅ አቅምና ተስፋ ሰጪ የልማት እንቅስቃሴዎች በግልጽ የታየ ሲሆን፤ እነዚህ ስትራቴጂካዊ የልማት ስራዎች የነዋሪዎቿን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ፣ የቱሪዝም እና የኢኮኖሚ መነቃቃትን የሚፈጥሩ መሆናቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል፡፡ እንዲሁም ከተማዋ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያላትን የንግድና የኢንቨስትመንት ማዕከልነት ሚና ይበልጥ የሚያጠናክሩ መሆናቸውን ነው የገለጸው። በተጨማሪም በአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት በቴክኖሎጂ ድጋፍ እየተካሄደ ያለውን ሪፎርምም ለማየት መቻላቸውን ጽህፈት ቤቱ አስታውቋል።
የአቪዬሽን መሠረተ ልማት ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልፅግና ምሰሶ ነው
Aug 6, 2026 222
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ) ፦ የአቪዬሽን መሠረተ ልማት ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልፅግና ምሰሶ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ዛሬ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የባሕር ዳር ደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አዲስ የመንገደኞች ማስተናገጃ ተርሚናል የአየር መንገዳችን ደማቅ የስኬት ጉዞ ማሳያ ነው ብለዋል። ይህ ዘመናዊ ተርሚናል ለባሕር ዳርና ለአካባቢው ፈርጀ ብዙ ኢኮኖሚያው ፋይዳ ያለው ከመሆኑም በላይ፣ ከተማዋን ከቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ቀጥሎ የሁለተኛው ትልቅ የዓለም አቀፍ አቪዬሽን ማዕከልነት ሚና እንዲኖራት የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ አገልግሎትን ተደራሽ ማድረግ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ የላቀ ጥራትን ማረጋገጥ ላይ ትኩረት አድርጎ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከፍተኛ የማስተናገድ አቅም እንዲኖረው ተደርጎ የተገነባው ይህ ደረጃውን የጠበቀ ተርሚናል፣ ተፈጥሯዊና ታሪካዊ ሀብቶችን ለመጎብኘት የሚመጡ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ቱሪስቶችን በቀጥታና በምቾት ለማስተናገድ በዕጅጉ እንደሚረዳም ነው የተናገሩት። በተጨማሪም የንግድና የኢንቨስትመንት ፍሰቱን በመጨመር ምርቶችን በፍጥነት ወደ ውጭ ገበያ ለመላክ፣ በአቪዬሽን፣ በሆቴልና በትራንስፖርት ዘርፎች ሰፊ የስራ ዕድል ለመፍጠር እንዲሁም ባሕር ዳርን የዓለም አቀፍ ስብሰባዎችና ሁነቶች ማዕከል ለማድረግ ከፍተኛ አቅምን እንደሚፈጥር አመልክተዋል። ፕሮጀክቶችን አቅዶ መጀመር፣ በጥራት ፈጽሞ ለህዝብ አገልግሎት ማብቃት የመደመር መንግሥት ባህልና መገለጫ መሆኑን የገለጹት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህ የትጋትና የመፈጸም ጉዟችን ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የውበት፣ የልምላሜና የፀዳል ተምሳሌት የሆነሽው ውቧ ባሕር ዳርና የአካባቢው ማህበረሰብ እንኳን ደስ አላችሁ! ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በባህር ዳር የተጀመሩ የኢኮኖሚና የመሰረተ ልማት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Aug 6, 2026 233
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 30/2018 (ኢዜአ)፦ባህር ዳር የልማትና የእድገት ምሳሌ ሆና እንድትቀጥል የተጀመሩ የኢኮኖሚና የመሰረተ ልማት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በባህርዳር ከተማ የደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተርሚናል ዛሬ መርቀው ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምርቃቱ ላይ ባደረጉት ንግግር ባህርዳር በተፈጥሮ ውበቷና በታሪካዊ እሴቶቿ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለጠቅላላው የአፍሪካ አህጉር የልማትና የእድገት ምሳሌ መሆን የምትችል ከተማ መሆኗን ገልጸዋል። ከተማዋ ከመቶ ዓመታት በፊት በሸዋ፣በወለጋ እና በጎንደር መካከል ይደረግ ለነበረው ከፍተኛ የንግድ እንቅስቃሴ እንደ ዋና መሸጋገሪያ ድልድይ ሆና ስታገለግል መቆየቷን ያወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ይህም ታሪካዊ አሰፋፈር ለክልሉ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ትልቅ መነሻ መሆኑን አስረድተዋል። በጎርጎራ እና በባህርዳር መካከል የነበረውን ጥንታዊ የንግድና የቱሪዝም ትስስር ለማጠናከር በርካታ ስራዎች መከናወናቸውን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣የጎርጎራ ሪዞርት እና የፈለገ ግዮን ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን በማሳያነት ጠቅሰዋል። በተጨማሪም እንደ ጣናነሽ ያሉ ትላልቅ መርከቦች በጣና ሀይቅ ላይ እንዲንቀሳቀሱ በማድረግ በሁለቱ አካባቢዎች ያሉ ታሪካዊ ደሴቶችንና ቅርሶችን ለጎብኚዎች ምቹ የማድረግ ስራ ከመንግስት አልፎ በግሉ ዘርፍም በትኩረት እየተሰራበት ይገኛል ነው ያሉት። ባህርዳር ከቱሪዝም በተጨማሪ በኢንዱስትሪው ዘርፍ ከፍተኛ እቅም ያላት በመሆኗ የኢንዱስትሪ ፓርክ እንደተገነባላትም ነው የጠቀሱት። ከተማዋ በሀገር ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀስ የውስጥ ለውስጥ መንገድ ዲዛይንና ግንባታ ያላት መሆኑን ጠቁመዋል። አክለውም በአካባቢው የተገነባው ታላቅ ድልድይ እና በአሁኑ ወቅት እየተካሄደ ያለው የኮሪደር ልማት ከተማዋን የበለጠ ውብና ለኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ምቹ የሚያደርጋት መሆኑን አብራርተዋል። በከተማዋ እየተገነባ ያለው ስታዲየም ሲጠናቀቅ ከሀገር ውስጥና ከአፍሪካ በርካታ ሰዎችን የሚስብ እንደሚሆንም ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተከናወነውን የሪፎርም ስራ አድንቀዋል። የፍርድ ቤቱ ፕሬዝዳንት ከቢሯቸው ሆነው በመላው ክልሉ የሚደረጉ ችሎቶችን በቨርቹዋል ለመከታተልና የህዝብን ቅሬታ ለመስማት የሚያስችል ዘመናዊ አሰራር በመዘርጋታቸው ምስጋና አቅርበውላቸዋል። አዲሱን የአውሮፕላን ማረፊያ ተርሚናል ግንባታ በተመለከተም፣ ቀድሞ የነበረው አሮጌ ተርሚናል በግጭት ምክንያት ጉዳት ቢደርስበትም፤ በችግሩ ከመበሳጨት ይልቅ አጋጣሚውን ወደ እድል በመቀየር ለቀጣይ ትውልድ የሚሻገር የተሻለና የላቀ ተርሚናል መገንባት መቻሉን ተናግረዋል። ይህ አሰራርና ችግርን ወደ መልካም አጋጣሚ የመቀየር ባህል ወደፊትም ሊደገምና ሊጠናከር እንደሚገባ አሳስበዋል። አዲሱ የደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ተርሚናል ከአብዛኞቹ የአፍሪካ ዋና ከተሞች ኤርፖርቶች የተሻለ አቅምና ደረጃ ያለው መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ይህንን ታላቅ እቅም ወደ ሙሉ ስኬት ለመቀየር የህዝቡ ትጋት፣ ጥረትና የጋራ ስራ አስፈላጊ በመሆኑ፣ህዝቡ ጊዜውንና እድሉን ተጠቅሞ ለልማት እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል። በተጨማሪም ሰላም ውድ ስጦታ፣ጊዜ ደግሞ ትልቅ ሀብት መሆኑን በማስገንዘብ፣ ህዝቡ በህብረት እንዲቆምና ሀገሩን እንዲያለማ ጠይቀዋል። ልዩነቶች ወይም አለመግባባቶች ቢኖሩ እንኳ እንደ ጨዋ ህዝብ በንግግርና በውይይት መፍታት እንደሚገባ፤ ነገር ግን በግጭት ጊዜ ማባከን እንደማይገባ በአፅንኦት አሳስበዋል። ባለፉት ሰላሳ ዓመታት ውስጥ ክልሉና ባህርዳር ከተማ ራሳቸውን ሙሉ በሙሉ የሚያስተዳድሩበት የተሟላ እድል አግኝተው እንደማያውቁ አውስተዋል። አሁን ግን በህግ በተሰጣቸው ስልጣን መሰረት መስራትና ማሰራትን የሚችሉ የክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሉ ገልጸው፣ሁሉም ተባብሮ ባህርዳርን እንዲያለማ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።