ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በአፋር ክልል የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ 
Aug 8, 2026 112
ሰመራ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦ በአፋር ክልል የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አወል አርባ ገለጹ። የአፋር ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 5ኛ የሥራ ዘመን፣ 10ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ ይገኛል።   ርዕሰ መስተዳድር አቶ አወል አርባ የክልሉን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ለምክር ቤቱ ባቀረቡበት ወቅት እንደተናገሩት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ ናቸው። በተለይም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራትን ማከናወን የተቻለ ሲሆን፤ በመስኖ ልማትም 142 ሺህ 675 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎችና አትክልቶች መሸፈን መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም መሠረት በበጀት ዓመቱ ከ5 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰብ መቻሉን አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅት የተለያዩ የግብርና ግብዓቶች መሰራጨታቸውን አመልክተው፤ ከዚህ ውስጥም ከ47 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጉን ገልጸዋል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በክልሉ ያልለሙ መሬቶችን ወደ እርሻ ሥራ በማስገባት የአርብቶ አደሩና ከፊል አርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ማስቻሉንም ነው ያብራሩት።   በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ከዚህ ቀደም ይስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን በማስወገድ በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከ16 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም አስረድተዋል። የብሔራዊ ዲጂታል መታወቂያን እስከ ታች ድረስ በማውረድና የንቅናቄ ሥራዎችን በማከናወን ከ405 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። ርዕሰ መስተዳድር አቶ አወል በሪፖርታቸው፤ በክልል ደረጃ 80 ሺህ 621 ዜጎች የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና መውሰዳቸውንም ነው ለምክር ቤቱ የገለጹት።
በሲዳማ ክልል የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማትን በማሻሻል ለሕዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Aug 8, 2026 102
ሀዋሳ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማትን በማሻሻል ለሕዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸው ተገለጸ። የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸሙን ገምግሟል። በመድረኩ የተገኙት የክልሉ የመንግሥት ረዳት ተጠሪ አቶ አሸናፊ ኤልያስ እንዳሉት፣ የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማትን በማሻሻል ለሕዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው። ከተማን ከወረዳና ከገጠር ቀበሌዎች የሚያገናኙ መንገዶችንና የአገልግሎት መስጫ ተቋማትን ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት መሰራቱን ጠቁመዋል። የክልሉ ከተሞች ለኑሮ፣ ለሥራና ለኢንቨስትመንት ምቹ እንዲሆኑ የኮሪደር ልማት ስራን በመስራት፣ የመኖሪያና የኢንቨስትመንት ቦታ በማቅረብ የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በከተሞችና በገጠር መካከል ያለውን የእድገትና የልማት ልዩነት ለማጥበብ በገጠር ኮሪደርና ሞዴል መንደሮችን የማስፋፋት ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አቶ አሸናፊ ተናግረዋል። የሲዳማ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ብሩክ ሰለሞን በበኩላቸው፣ የክልሉ ከተሞች ደረጃውን በጠበቀ ፕላን እንዲመሩ ለማድረግ በተከናወነው ሥራ የ73 ከተሞች የፕላን ክለሳና አዲስ ፕላን የማዘጋጀት ሥራ መሰራቱን ጠቁመዋል። በከተሞች የአገልግሎት አሰጣጡን ከማሻሻል አኳያ በሐዋሳ በክልሉና በከተማ አስተዳደሩ «መሶብ» የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ወደ ስራ በማስገባት ቀልጣፋ አገልግሎት መስጠት መቻላቸውን ገልጸዋል። ይህን ለማስፋት በስድስት ከተሞች የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ማዕከላት ግንባታ ተጠናቆ የቁሳቁስ የማሟላት ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰው፣ በተያዘው የ2019 በጀት ዓመት ወደ ሥራ እንዲገቡ ይደረጋል ብለዋል። የወንዶገነት ወረዳ ኮንስትራክሽን ባለሥልጣን ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መልካሙ ኤርሚያስ እንዳሉት፣ በወረዳው በከተማና በገጠር መካከል ያለውን የልማት ልዩነት ለማመጣጠን እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። በወረዳው የገጠር ኮሪደር ልማትና ሞዴል የገጠር መንደሮችን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተከናወነ ተግባር 13 ሞዴል ቤቶችን መገንባት እንደተቻለ ገልጸዋል። ወንዶገነት በወሻ ከተማ አቅራቢያ ያሉ የተፈጥሮ ፍልውኃዎችን በአግባቡ አልምቶ የቱሪስት ፍሰቱንና ገቢን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። የሴክተሩ የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ ላይ የክልሉ አራት ዞኖች ዋና አስተዳዳሪዎች፣ የሐዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ፣ የወረዳ አመራሮችና የሴክተሩ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል።    
የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ አሲዳማ መሬትን የማከም ተግባር እያከናወነ ይገኛል
Aug 8, 2026 170
ቴፒ፤ ነሐሴ 02/2018 (ኢዜአ)፦ የቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ የሚያስችል አሲዳማ መሬትን የማከም ተግባር እያከናወነ መሆኑን አስታወቀ። ማዕከሉ በምርምር አዳዲስ ዝርያዎችን ከማውጣትና ከማላመድ ባሻገር የአፈር አሲዳማነት ቁጥጥርና ማከም ተግባራትን በማከናወን ለአርሶ አደሮች ችግር ፈቺ መፍትሔዎችን እያቀረበ መሆኑን ገልጿል። የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር ደረጀ ቱሉ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ የአርሶ አደሩን የግብርና ሥራ ውጤታማነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት ምርታማነትን የሚቀንሱ ምክንያቶችን በጥናት ተከታትሎ ማስወገድ ይገባል። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦችና በጋምቤላ ክልሎች በአሲዳማነት የተጠቃ ሰፊ ማሳ መኖሩን ጠቅሰዋል። "ይህም ምርታማነትን በመቀነስ በአርሶ አደሩ ላይ የሚያሳድረውን አሉታዊ ተጽዕኖ ለመግታት አሲዳማ መሬትን የማከም ሥራ እየሠራን ነው" ብለዋል። በዘንድሮው ዓመት በክልሉ ከ100 ሄክታር በላይ ማሳ የማከም ተግባር መከናወኑን ገልጸው ከዚህ ውስጥ በየኪ ወረዳ 22 ሄክታር ማሳ ምርት አያያዝ ውጤታማ ሆኖ መገኘቱን አስረድተዋል። ማዕከሉ አሲዳማ አፈርን በመመርመር በኖራ፣ በቨርሚ ኮምፖስት እንዲሁም በኖራና በተፈጥሮ ኮምፖስት ቅይጥ የማከም ሥራ የሚሠራ ሲሆን፣ በቀጣይም ይህን ተግባር በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ይሠራል ብለዋል። የአፈር አሲዳማነት በይበልጥ በበቆሎ ምርት ላይ ጉዳት የሚያደርስ በመሆኑ ከአንድ ሄክታር ከ20 ኩንታል ያነሰ ምርት እንዲሰጥ እንደሚያደርግ በማዕከሉ የአፈር ለምነት ተመራማሪ ሙሉሰው ወዳጆ ተናግረዋል። ዝናብ በሚበዛባቸው አካባቢዎች ጎልቶ የሚታየው አሲዳማ መሬት ከታከመ በኋላ ከ70 ኩንታል በላይ የበቆሎ ምርት ወደ መስጠት ደረጃ ተመልሶ እንደሚያገግም ገልጸዋል። የየኪ ወረዳ ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ኅብረት ሥራ ጽሕፈት ቤት የአዝርዕትና ሰብል ልማት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ይርጋለም አሰፋ በዞኑ በቆሎ በተስማሚነት የሚለማ ቢሆንም፣ በአሲዳማ አፈር ስለሚጠቃ ምርታማነቱ አነስተኛ መሆኑን ጠቁመዋል። በምርምር ማዕከሉ የታከመው ማሳ ያመጣውን ውጤት በቀጣይ በሌሎች ማሳዎች ወደተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ለማስፋት ትኩረት አድርገው እንደሚሠሩ ገልጸዋል። ከአካባቢው አርሶ አደሮች መካከል የአዲስዓለም ቀበሌ አርሶ አደር መሐመድ ሰኢድ እና ሰሎሞን ኃይሌ፣ የግብርና ምርምሩ ማሳቸውን በኖራ አክሞ ተስፋቸው እንዳለመለመ ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በቆሎ ሲዘሩ ግማሹ ሳይበቅል የሚቀርበትና የበቀለውም እየቀጨጨ የሚበላሽበት ሁኔታ ይገጥማቸው እንደነበር ገልጸው አሁን ላይ ማሳው ታክሞ የዘሩት በቆሎ ምርት አያያዝ ከቤተሰብ ፍጆታ ተርፎ ለገበያ መብቃት የሚችል መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም ሌሎች ማሳዎቻቸውን በማሳከም ምርታማነታቸውን ለማሳደግ ጠንክረው እንደሚሠሩም አርሶ አደሮቹ ተናግረዋል። በየኪ ወረዳ አዲስ ዓለም ቀበሌ 22 ሄክታር አሲዳማ መሬት በኖራ ታክሞ 86 አርሶ አደሮች በኩታ ገጠም ያለሙት የበቆሎ ማሳ ውጤታማነት ተሞክሮ ለሌሎች እንዲጋሩ እየተደረገ መሆኑም ተመላክቷል።
የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽንና የሪፖርታጅ ግሩፕ የልማት ትብብር የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ዘርፉን ለማዘመን ተጨማሪ አቅም ይፈጥራል
Aug 8, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽንና የሪፖርታጅ ግሩፕ የልማት ትብብር የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ዘርፉን ለማዘመን ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር መሆኑን የመከላከያ ሚኒስትር ዴኤታ ማርታ ሉዊጂ ገለጹ። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ከዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ ሪፖርታጅ ግሩፕ ጋር በመተባበር በአዲስ አበባ ሁለገብ የመኖሪያና የንግድ ሕንፃ ለመገንባት የልማት አጋርነት ፕሮጀክት ይፋ አደረጉ። የመከላከያ ሚኒስትር ዴኤታ ማርታ ሉዊጂ በዚህ ወቅት፣ አጋርነቱ የተቋማቱን ስትራቴጂያዊ የልማት አጋርነት በማጠናከር የኢትዮጵያና ዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ ትብብርን የሚያሳድግ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የሀገራቱን ጠንካራ ስትራቴጂያዊ አጋርነት ወደ ላቀ ምዕራፍ ለማሸጋገር የሚያስችል ጭምር እንደሆነም ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ ዘመናዊ ከተማን በመገንባት የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ለማጠናከር ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አመልክተዋል። የፋውንዴሽኑና የሪፖርታጅ ግሩፕ ትብብርም ዓለም አቀፍ አልሚዎች ኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት መዳረሻ የስበት ማዕከል እያደረጓት እንደሚገኝ ማሳያ ነው ብለዋል። የሪፖርታጅ ግሩፕ ሊቀመንበር አሪፍ ኢስማኤል በበኩላቸው ፕሮጀክቱ በሀገራቱ መካከል ያለውን ሁለንተናዊ የልማት ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑን ገልጸዋል። የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሜጀር ጄኔራል ደረጀ መገርሳ፣ ፕሮጀክቱ ከአዲስ አበባ ፈጣን የከተሜነት ዕድገት ጋር የሚመጣጠን ዘመናዊ ግንባታ እንደሚሆን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ ለሠራዊቱ የመኖሪያ ቤት ፍላጎት ለማሟላት ተጨማሪ የገቢ አቅም የሚገነባ መሆኑን አመልክተዋል። የሪፖርታጅ ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሐናን አሕመድ ኑር እንዳሉት፤ በአፍሪካ ሕብረት ዋና መሥሪያ ቤት ፊት ለፊት በ23 ሺህ ካሬ ሜትር የሚገነባውን ፕሮጀክት በሦስት ዓመታት ጊዜ ለማጠናቀቅ ይሰራል ብለዋል። ሕንፃው 1 ሺህ 86 ስቱዲዮ፣ ባለአንድና ባለሁለት መኝታ የመኖሪያ አፓርታማ፣ የንግድ ሱቆች፣ ጂምናዚየም፣ መዋኛ ገንዳ፣ የስፖርት ማዘውተሪያና ሌሎች ዘመናዊ አገልግሎቶችን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱም በመኖሪያና በንግድ ልማት ብቻ ሳይወሰን ለኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ዘርፍ ዘመናዊነት፣ የሥራ ዕድል ፈጠራና ለኢንቨስትመንት መስፋፋት አዲስ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
በሀገሪቱ እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ በትብብርና በቅንጅት መስራት ይገባል
Aug 8, 2026 135
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦ የኢንቨስትመንቱን ዘርፍ በማጠናከር እንደ ሀገር እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ የትብብርና የቅንጅት ስራዎች ሊጠናከሩ እንደሚገባ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። በሀገር አቀፍ ደረጃ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተከናወኑት ሥራዎች ከ4 ነጥብ 44 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን አስታውቋል። የፌዴራል፣ የክልልና የከተማ አስተዳደሮች የኢንቨስትመንት አስፈጻሚዎች የጋራ ሀገራዊ የምክክር መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ መካሄድ ጀምሯል።   ርዕሰ መስተዳድሯ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ እንደ ክልል ብሎም እንደ ሀገር ሰፊ የኢንቨስትመንት አማራጮች አሉ፤ እነዚህንም ልማት ላይ ማዋል ይገባል። በዚህም እየተመዘገበ ያለውን የኢኮኖሚ እድገት ቀጣይነት ለማረጋገጥ በፌዴራልና በክልሎች የተጀመሩ የትብብርና ቅንጅታዊ አሠራሮች ይበልጥ ሊጠናከሩ ይገባል ብለዋል። በክልሉ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በኢንቨስትመንት ዘርፉ በተከናወኑት ሥራዎች በርካታ ባለሀብቶች ወደ ክልሉ በመግባት በዘርፉ እየተሳተፉ እንደሚገኙና ተጨባጭ ውጤትም እየተመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በቀጣይም በክልሉ ያሉትን የግብርና፣ የማዕድን፣ የቱሪዝምና ሌሎች የኢንቨስትመንት አማራጮች ምቹ በማድረግ ለዘርፉ መጠናከር የክልሉ መንግሥት በትኩረት እንደሚሠራ ነው ያረጋገጡት። የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ዳጋቶ ኩምቤ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ ኮሚሽኑ የተጣለበትን ሀገራዊ ኃላፊነት ለመወጣት ባከናወናቸው ተግባራት አበረታች ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል።   በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዘርፉ በተከናወኑት ሥራዎች ከ4 ነጥብ 44 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ መቻሉን ጠቁመዋል። ይህም ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ8 ከመቶ በላይ ብልጫ ያለው መሆኑን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ አበረታች ውጤቶችን ማስመዝገብ የተቻለው የፌዴራልና የክልል ባለድርሻ አካላት ያደረጉት ያልተቆጠበ የተቀናጀ ጥረት ውጤት መሆኑንም ተናግረዋል። በቀጣይም የትብብርና የቅንጅታዊ ሥራዎችን በማጠናከር በዘርፉ የተገኙትን ስኬቶች ይበልጥ ለማስፋት እንደሚሠራ ምክትል ኮሚሽነሩ ገልጸዋል። የጋምቤላ ክልል ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሎው ኡቡፕ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በክልሉ ባሉት የኢንቨስትመንት አማራጮች የባለሀብቶች ተሳትፎ እንዲጠናከር በማድረግ ረገድ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል ብለዋል።   በቀጣይም ከምክክር መድረኩ የሚገኙ ተሞክሮና ልምዶችን በማስፋት ለዘርፉ ውጤታማነት በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል። ከዛሬ ጀምሮ ለሁለት ቀናት በሚቆየው የምክክር መድረክ የፌዴራል፣ የክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች የኢንቨስትመንት አስፈጻሚዎች በ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸምና በአዲሱ በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ በመወያየት የጋራ አቅጣጫ ያስቀምጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።
በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል
Aug 8, 2026 284
ሆሳዕና፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተከናወነው የፍራፍሬ ልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበበት መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአካባቢ ጥበቃን ከማረጋገጥ ባሻገር የፍራፍሬ ልማትን በማስፋፋት የዜጎችን የምግብ ዋስትና እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደገ ይገኛል። መርሃ ግብሩ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም በሚደረገው ጥረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማበርከት የሀገሪቱን የደን ሽፋን በተጨባጭ እያሳደገ መሆኑ እሙን ነው።   የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ የተራቆቱ መሬቶችን በማልማትና ለቀጣዩ ትውልድ ምቹ አካባቢን በመፍጠር ረገድ ውጤታማነቱን እያስመሰከረ ይገኛል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡስማን ስሩር እንደገለጹት፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በፍራፍሬ ልማት የምግብ ዋስትናውን ያረጋገጠና ተጠቃሚነቱን ያሳደገ ቤተሰብ መፍጠር ተችሏል።   የአረንጓዴ አሻራ ትግበራው ለምግብነት የሚውሉ ዛፎችን በመትከል ረገድ ተቋማትን ጨምሮ የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማሳደግ ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረዋል። መርሃ ግብሩ ክልሉ በፍራፍሬ ልማት ያለውን አቅም በአግባቡ እንዲጠቀም ያደረገ ሲሆን የማህበረሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማሳደግ ረገድም ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበበት እንደሚገኝ አስረድተዋል። በሀድያ ዞን የምስራቅ ባደዋቾ ወረዳ ዌራቡሼራ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር ኤልያስ መጋቦ በበኩላቸው፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 1 ነጥብ 5 ሄክታር የተራቆተ ማሳቸውን አልምተው ለመጠቀም መቻላቸውን ገልጸዋል።   ማሳቸውን በአቮካዶ፣ በሙዝ፣ በሌሎች የፍራፍሬና የቅመማ ቅመም ሰብሎች በማልማትም ውጤታማ መሆን መቻላቸውን ተናግረዋል። በዚህም ምርትና ምርታማነታቸው እያደገ በመምጣቱ ያመረቱትን ከቤተሰብ ፍጆታ አልፎ ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንዳሳደጉ ገልጸዋል። የሆሳዕና ከተማ የሄጦ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ትግስት አጋፋሪ፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተሳትፎ በማድረግ በውስን መሬት ላይ ለምግብነት የሚውሉ ችግኞችን ማልማታቸውን ነው የሚናገሩት።   ከዚህ ውስጥም የተከሉት የአቮካዶ ችግኝ ደርሶ ፍሬ መስጠት በመጀመሩ ያገኙትን ምርት ከቤት ውስጥ ፍጆታ አልፎ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ እንደሚገኙ አስረድተዋል።
 የኢትዮጵያ የስንዴ ምርታማነት ዕድገት የአፍሪካን የምግብ ሉዓላዊነት ማረጋገጥ የሚያስችል ተምሳሌታዊ ተሞክሮ ነው 
Aug 8, 2026 305
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦የኢትዮጵያ የስንዴ ምርታማነት ዕድገት የአፍሪካን የምግብ ሉዓላዊነት ማረጋገጥ የሚያስችል ተምሳሌታዊ ተሞክሮ መሆኑን የቀድሞ የአፍሪካ ሕብረት የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ጉዳዮች ኮሚሽነር ጆሴ ፋል ሊዮኔል ኮሪያ ሳኩ ገለጹ። የአፍሪካ ሀገራትም የኢትዮጵያንና ሌሎች ምርጥ ተሞክሮዎችን በመቀመር በግብርናው መስክ የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጥ የራስ አቅም መገንባት እንዳለባቸው አሳስበዋል። ጆሴፋ ሊዮኔል ኮሪያ ሳኮ ለኢዜአ እንዳሉት፤ አፍሪካ ግብርናን ጨምሮ የምግብ ሉዓላዊነትንና የምርታማነት አቅምን የሚያጎለብት በርካታ የዕድገት ተስፋና ጸጋ የታደለች አህጉር ናት። በዚህም የአፍሪካን እምቅ የዕድገትና የብልፅግና ተስፋዎች ወደ ዕድል በመቀየር የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ የግብርና ምርታማነትን ማጎልበት እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።   የአህጉሪቷ የግብርና ምርታማነት እምቅ አቅምና ጸጋም የአፍሪካውያንን የምግብ ዋስትና በራስ አቅም በመሸፈን ከጥገኝነት መላቀቅ የሚያስችል የተቀናጀ ትብብርና ጥረት ማድረግን እንደሚጠይቅ አስረድተዋል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ስምምነትም የአህጉሪቱን የእርስ በርስ ንግድ በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማጠናከር፣ ረሃብንና ድህነትን ለመቀነስ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። አፍሪካ ሙሉ በሙሉ በውጭ እርዳታ ላይ ከመመስረት ይልቅ የራሷን ሀብትና አቅም በመጠቀም ፕሮጀክቶችን በውጤታማነት ማከናወን እንደሚገባትም አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ የግብርና ምርታማነትና የአካባቢ ጥበቃ ስኬቶች ለአፍሪካ የዕድገት ተስፋ ተምሳሌት መሆናቸውን አብራርተዋል። በተለይም በበጋ መስኖና በተለያዩ የመኸር ወቅቶች የስንዴ ምርታማነትን በማሳደግ፣ ከውጭ ምርት ጥገኝነት በመላቀቅ ለውጭ ንግድ የሚተርፍ አቅም መገንባቷ የሚደነቅ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አጠቃላይ የግብርና፣ የአካባቢ ጥበቃና የከተማ ልማት እመርታዊ ስኬቶችም የአፍሪካን የዕድገት ተስፋ ለመቅረጽ እንደ ልምድና ተሞክሮ ሊወሰዱ የሚችሉ መሆናቸውን አንስተዋል።   በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርና በከተሞች መሠረተ ልማት ማዘመን ያከናወነቻቸው ተግባራትም ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ከኢትዮጵያ ተሞክሮ ሊማሩና ሊጋሩት የሚገባ ወሳኝ የልማት አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል። የአረንጓዴ ዐሻራም የአካባቢ ሚዛንን ከመጠበቅ ባሻገር የኢትዮጵያን አረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ለማሳለጥ አቅም እንደሚፈጥር ጠቁመዋል። በዚህም የአፍሪካ ሀገራት በግብርና፣ በአካባቢ ጥበቃና በከተሞች ልማት ዘርፎች የተሳኩ ተሞክሮዎችን በመለዋወጥና በተቀናጀ መንገድ በመስራት የአህጉሪቱን ዘላቂ ዕድገት ማጠናከር እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በአማራ ክልል በመኸር እርሻ 5 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በዘር ተሸፍኗል
Aug 8, 2026 153
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦በአማራ ክልል በመኸር እርሻ 5 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በዘር መሸፈኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የሰብል ልማት ማስፋፊያ ባለሙያ ወይዘሮ እንየ አሰፋ እንደገለጹት፤ በተያዘው የክረምት ወቅት የመኸር እርሻ 5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል። በዚህም እስካሁን ከ5 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በዘር በመሸፈን የእቅዱን 91 በመቶ ማሳካት ተችሏል ብለዋል። እቅዱን ሙሉ ለሙሉ ለማሳካትም ጤፍ፣ ሽንብራና ሌሎች ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን በመዝራት በአጠቃላይ 205 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማምረት ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህ ውስጥ ከ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም የለማ ሲሆን በመስመር መዝራትና ሌሎች አዳዲስ አሰራሮች መተግበራቸውንም አስረድተዋል። በተጨማሪም ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል 2 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ማዳበሪያ እስካሁን ጥቅም ላይ መዋሉን አረጋግጠዋል። በደቡብ ጎንደር ዞን ፎገራ ወረዳ ቋር ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ወንድምሁነኝ ዘለቀ እንደገለጹት፤ በክረምቱ አንድ ሄክታር ተኩል መሬታቸውን በሩዝ ሰብል በመሸፈን የመንከባከብ ስራ እየሰሩ ይገኛሉ። ምርታማነቱን ለማሳደግም 2 ኩንታል ማዳበሪያ ተጠቅመው መዝራታቸውን ጠቁመው፣ ከዘሩት ማሳ ላይ 75 ኩንታል የሩዝ ምርት ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በባህር ዳር ከተማ ዘንዘልማ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር ከፍያለው ንጉሴ በበኩላቸው፤ ለመኸር እርሻ አስፈላጊ ግብአቶችን በማግኘታቸው ከ5 ሄክታር በላይ በሆነ መሬታቸው ሩዝ፣ ዳጉሳ፣ ማሽላና ጤፍ ማልማታቸውን ተናግረዋል። ከዚህም ከ130 ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠብቁ ነው የተናገሩት። በክረምቱ ወቅት እየተካሄደ ባለው የሰብል ልማት ስራ ከአራት ሚሊዮን በላይ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ እንደሚገኙ ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምክንያታዊና ፍትኃዊ የውሃ ሀብት አጠቃቀምን መሰረት ያደረገ  ነው 
Aug 8, 2026 183
አርባ ምንጭ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ) ፦የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምክንያታዊና ፍትኃዊ የውሃ ሀብት አጠቃቀምን መሰረት ያደረገ መሆኑን የዘርፉ ምሁራን ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብና መንግስት የግብጽን ሴራና ተጽዕኖ በመቋቋም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን እንዳሳኩት ሁሉ የባህር በር ባለቤትነትም ተገቢ ምላሽ እንዲያገኝ የጋራ አቋም ይዘው ለማሳካት እየተንቀሳቀሱ ነው። ኢዜአ በጉዳዩ ላይ ያነጋገራቸው የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ለሀገር ሁለንተናዊ የዕድገት መሰረት እንደሆነ ተናግረዋል። ከምሁራኑ መካከል በዩኒቨርሲቲው የውሃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የውሃ ሀብት ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር ኤልያስ ገበየሁ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያ ያላትን የውሃ ሀብት አልምታ የመጠቀም መብት አላት። ስታራምደው የነበረው በፍትሃዊነት ላይ የተመሰረተ የውሃ ሃብት አጠቃቀምና በጋራ የመልማት ጽኑ አቋምም ሁሉን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን አንስተዋል፡፡ ይሁንና በውሃ ሀብቷን በፍትሃዊነት እንዳትጠቀም በተለያዩ አካላት በተለይ በግብጽ በተለያየ መንገድ ጫና ሲደረግባት መቆየቱን ኤልያስ (ዶ/ር) ገልጸዋል። በዚህም የቅኝ ግዛት የውሃ ስምምነቶችን መሰረት በማድረግ ግብጽ በዓባይ ወንዝ አጠቃቀም ላይ ለዘመናት የነበራትን የበላይነት ለማስቀጠል ከነበራት ጽኑ ፍላጎት የሕዳሴው ግድብ እንዳይገነባ ከጅምሩ አንስቶ ለማስተጓጎል ስትጥር ቆይታለች። ይህን የግብጽ ሴራ በማክሸፍ ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን አልምታ በፍትሀዊነት እንድትጠቀም መንግስትና ህዝብ በተባበረ ክንድ ባከናወኑት ስኬታማ የዲፕሎማሲ ሥራ እና ለግንባታው ባሳዩት ቁርጠኝነት ሴራውን በማክሸፍ ግድቡን እውን ማድረግ ተችሏል። በዚህም ኢትዮጵያ በውሃ ሀብቷ የመልማት መብቷን በተግባር ማረጋገጧን የገለጹት ምሁሩ፣ አሁንም ኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤት እንዳትሆን ግብጽ በተለያየ መንገድ እያሴረች መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣናው ሀገራት በትብብር የመልማት መርህን ወደጎን ያለውና በግብጽ ሴራ ጭምር ከቀይ ባሕር እንድንርቅ የተደረገበት ይህ እኩይ ተግባር የኢትዮጵያን ታሪካዊና ሕጋዊ መብት የጣሰ መሆኑንም አንስተዋል። በታሪክም ኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤት የነበረችና ከቀይ ባህር ጋር የነበራት ትስስርም የቆየ እንደሆነ ምሁሩ አመልክተዋል። ምሁሩ አክለውም ኢትዮጵያውያን በባህር በር ላይ የጀመሩትን የጋራ አቋም ካጠናከሩ ይህን ሴራዋን ማክሸፍ ይቻላል ብለዋል። በዩኒቨርሲቲው መምህርና በውሃ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የውሃ ሀብት እና ምህንድስና ፋካልቲ ተመራማሪ ሳሙኤል ዳጋሎ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ከዓባይ ወንዝ አጠቃቀም ጋር በተያያዘ ኢትዮጵያን ያገለለውና የውሃ ሀብቷን እንዳትጠቀም በሴራ የተዘጋጁ የቅኝ ግዛት ውሎች የአንድ ወገን ተጠቃሚነትን ብቻ ያረጋገጡ መሆናቸውን አንስተዋል። ሁሌም ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም በተጻራሪ የምትቆመው ግብጽ ዛሬም ኢትዮጵያ የባህር በር እንደተቆለፈባት እንድትኖር ብርቱ ጥረት እያደረገች መሆኗን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ለዘመናት የባሕር በር ባለቤት መሆኗን አስታውሰው፤ ለኢትዮጵያ የባሕር በር የህልውና ጉዳይና የሕዝብ ጥያቄ መሆኑን አስረድተዋል። ይሁንና ዛሬም ከቅኝ ግዛት አስተሳሰብ አዙሪት ያልወጣችው ግብፅ በሕዳሴው ግድብ ያላሳካችውን ሴራ በቀይ ባህር ለማሳካት እያካሄደች ያለው ዘመቻ ተቀባይነት የለውም ብለዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለድርድር እንደማይቀርብና ከዓለም አቀፍ ደኅንነት ጋር ጭምር እንደሚገናኝ ምሁሩ አያይዘው ገልጸዋል።
የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ያስመዘገበውን ለውጥ ማጠናከር ይገባል - ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ
Aug 7, 2026 439
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ያስመዘገበውን ለውጥ ማጠናከር እንደሚገባ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ገለጹ። ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ስር እየተካሄዱ ያሉ የአዳማ ጋርመንትና ኢንዱስትሪ፣ የጋሻ የሠራዊቱ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ፕሮጀክት እና የመከላከያ ባጅና ሜዳሊያ ማምረቻ ፋብሪካን ጎብኝተዋል።   በጉብኝቱ ወቅት የአዳማ ጋርመንት ኢንዱስትሪ ያስገነባውን አዲስ የማስፋፊያና የማሻሻያ ፕሮጀክት መርቀው ከፍተዋል። ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በጉብኝታቸው ወቅት፣ የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን አመራሮችና ሠራተኞች ላስመዘገቡት ውጤት በማመስገን የተገኘው ለውጥ ሳያዘናጋቸው ለበለጠ ውጤት እንዲተጉ አሳስበዋል። በቀጣይም የምርት ጥራትን በማሻሻል፣ የምርምርና የቴክኖሎጂ ልማትን በማስፋፋት፣ የዲጂታላይዜሽን ሥራዎችን በማጠናከር፣ የግብዓት አቅርቦትን በራስ አቅም በማሳደግ በአፍሪካ ደረጃ ተወዳዳሪ ኢንዱስትሪ እንዲገነባ አቅጣጫ ሰጥተዋል። ሠራዊቱ መለኪያው ሀገሩ ነው ያሉት ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ፣ የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን የተቋሙንና የሀገራችንን ፍላጎት በማሳካት ያለውን ሚና ይበልጥ ማጠናከር ይገባል ብለዋል።   በጉብኝቱ ላይ የአዳማ ከተማ ከንቲባን ጨምሮ የመከላከያ ሠራዊት ከፍተኛ አመራሮች እና የፋውንዴሽኑ የሥራ ኃላፊዎች መገኘታቸውን የመከላከያ ሠራዊት ማኅበራዊ ትሥሥር ገጽ መረጃ አመላክቷል።
በሲዳማ ክልል የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኢንዱስትሪ ልማት መስፋፋት ምቹ መደላድል ፈጥሯል
Aug 7, 2026 384
ሃዋሳ፣ ነሀሴ1/2018(ኢዜአ)፡-በሲዳማ ክልል የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኢንዱስትሪ ልማት መስፋፋት ምቹ መደላድል መፍጠሩን የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ ገለጹ። የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ የ2018 በጀት አመት አፈጻጸምና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በሃዋሳ ከተማ ተካሂዷል።   በመድረኩ የተገኙት የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ እንደገለጹት በክልሉ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለኢንዱስትሪ ልማት መስፋፋት ምቹ መደላድል ፈጥሯል። ይህም የኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም በማሳደግ ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባሻገር ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ የመተካት አቅምን እያሳደገ መሆኑን ጠቁመዋል። በቀጣይም የኢንዱስትሪዎችን የማምረት አቅም ይበልጥ ለማሳደግ መስረተ ልማቶችን በቅንጅት የማሟላት ሥራው በቀጣይም ይጠናከራል ብለዋል።   የክልሉ ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ አሻግሬ ጀምበሬ በበኩላቸው በክልሉ የኢንዱስትሪ አቅምን በማጠናከር የማምረት አቅምን የማሳደግ፣ የስራ ዕድል የመፍጠር፣ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን መጠን የመጨመርና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ የመተካት ሥራ በትኩረት መከናወኑን ጠቁመዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ249 በላይ አዳዲስ ኢንዱስትሪዎችን ወደ ሥራ የማስገባትና ነባሮቹን በመደገፍ ከ22 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩንም ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ ከክልሉ 14 ሺህ 500 ቶን የኢንዱስትሪ ምርቶችን ወደ ውጭ በመላክ 155 ሚሊዮን ዶላር ገቢ መገኘቱንም አቶ አሻግሬ ጠቅሰዋል። በተመሳሳይ 290 ሚሊዮን ዶላር የሚገመቱ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካት ተችሏል ብለዋል።
በሲዳማ ክልል አርሶ አደሩን ከእንስሳት ልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ሆነዋል
Aug 7, 2026 268
ይርጋለም፤ ነሀሴ 1/2018 (ኢዜአ)፡-አርሶ አደሩን ከእንስሳት ልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ በመኖ አቅርቦትና ጤና አጠባበቅ ላይ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን የሲዳማ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሀም ማርሻሎ ተናገሩ። የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ የ2019 በጀት ዓመት የእንስሳት መኖ ልማትና የበሽታ መከላከያ ክትባት ሥራዎች ይፋዊ ማስጀመሪያ መርሀግብር በይርጋዓለም ከተማ ተካሂዷል።   ‎በመርሀግብሩ ላይ የሲዳማ ክልል የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሀም ማርሻሎ በክልሉ የአርሶ አደሩን ከእንስሳት ልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የተከናወኑ የመኖ አቅርቦትና ጤና አጠባበቅ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። ዘመናዊ የእንስሳት እርባታ ዘዴው ‎ለእንስሳት ዝርያ ማሻሻል፣ ለመኖ አቅርቦትና ለጤና አጠባበቅ ሥራ ከፍተኛ እገዛ ማድረጉንም ገልጸዋል። ‎አርሶ አደሩ የመኖ አቅርቦቱን ከሌማት ቱሩፋት ሥራ ጋር በማቀናጀትና የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማነቱን ማሳደጉን ጠቁመዋል። የክልሉ መንግስት የአርሶ አደሩን ከእንስሳት ልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ ከሚያደርገው ሞያዊ እገዛ በተጨማሪ የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎችን ማቅረቡን አንስተዋል።   የክልሉ እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰፋ ፎና በክልሉ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር ከመጀመሩ በፊት 170 ሺህ የነበረው የተሻሻሉ የዳልጋ ከብቶች ቁጥር በአሁኑ ወቅት ወደ 600 ሺህ ለማሳደግ መቻሉን አብራርተዋል። ይህም የክልሉን የእንስሳትና እንስሳት ተዋጽኦ ከማሳደግ ባለፈ የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት መሳደጉን አንስተዋል። ከዚህ በተጓዳኝም የእንስሳት መኖ አቅርቦትን ለማስፋት በተደረገ ጥረት በበጀት ዓመቱ ከ32 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ልማቱ መካሄዱን ጠቁመዋል። በክልሉ የእንስሳት ጤናን ለመጠበቅም የበሽታ መከላከልና ክትባት ሽፋኑንለማሳደግ በቅንጅት መሰራቱን አስረድተዋል። ይህም የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር ለማሳካትና የአርሶ አደሩ ተጠቃሚነት ከማሳድግ ባለፈ ለኢንዱስትሪዎች ግብአት ለማቅረብ አስችሏል ብለዋል።   በይርጋዓለም ከተማ ጋኔ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ደረጀ ሙጤ የተሻሻሉ ዝርያ ያላቸው የወተት ላሞች በማርባት ወተትና የወተት ተዋጾን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለእንስሳቱም በግማሽ ሄክታር መሬታቸው ላይ የመኖ ሣር በማልማት ውጤታማነታቸውን ለማጉላት እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ‎የእንስሳቱን ምርታማነት ለማሳደግ የምጥን መኖ አቅርቦትና ጤናቸውን መከታተል ላይ የባለሞያ ድጋፍ ማግኘታቸውንም ጠቁመዋል።   በማስጀመሪያ መርሀ ግብሩ ላይ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደን ጨምሮ የክልል፣ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች የተገኙ ሲሆን በይርጋለም ከተማም የተለያዩ የሌማት ትሩፋት ስራዎች ተጎብኝተዋል።          
የደጃዝማች በላይ ዘለቀ አውሮፕላን ማረፊያ አዲስ ተርሚናል የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ፍሰቱን ያቀላጥፋል
Aug 7, 2026 273
ባህር ዳር ፤ነሐሴ 1/2018(ኢዜአ)፡- የደጃዝማች በላይ ዘለቀ አውሮፕላን ማረፊያ አዲስ ተርሚናል የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ፍሰቱን እንደሚያቀላጥፍ በዘርፉ የተሰማሩ ግለሰቦች ገለጹ። በባህር ዳር ከተማ የደጃዝማች በላይ ዘለቀ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በአዲስ የተገነባውን ተርሚናል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መመረቃቸው ይታወሳል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ በባህር ዳር የተገነባው ተርሚናል በኢትዮጵያ ከቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ቀጥሎ ግዙፉ ተርሚናል መሆኑን መግለጻቸው አይዘነጋም። አስተያየት ሰጪዎች እንዳሉት የአውሮፕላን ማረፊያው ተርሚናል በአዲስ መልክ መገንባቱ የከተማዋን የቱሪዝም፣ የኢንቨስትመንትና የንግድ እንቅስቃሴ ለማፋጠን ያስችላል ብለዋል። የባህር ዳር አስጎብኚዎች ማኅበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ማስተዋል ዘለቀ እንደገለጹት፤ የተርሚናሉ ዓለም አቀፍ ደረጃውን ጠብቆ መገንባት የቱሪዝም ዘርፉን ዕድገት የሚያፋጥን ነው። ባህር ዳር በጣና ሐይቅ የሚገኙ ገዳማትን፣ የጢስ አባይ ፏፏቴንና ሌሎች በውስጧ የሚገኙ የመስህብ ሀብቶችን ለመጎብኘት የሚመጡ እንግዶችን በማስተናገድ የምትታወቅ ከተማ መሆኗን ገልጸዋል። በተጨማሪም ወደ ጎንደር፣ ላሊበላና ሌሎች የቱሪስት መስህብ ስፍራዎች ለመጓዝ ለሚመጡ የውጭና የሀገር ውስጥ ጎብኚዎች ዋነኛ መተላለፊያ በመሆን እያገለገለች ትገኛለች ብለዋል። ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ተርሚናል መገንባቱም ወደ ከተማዋ የሚመጡ ቱሪስቶችን ምቾትና ደህንነት በመጠበቅ የሀገራችንን ገጽታ ለመገንባት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። ሌላው በአስጎብኚነት ሥራ የተሰማሩት አቶ አበበ ያረጋል በበኩላቸው፤ ግዙፍና ዘመናዊ ተደርጎ የተገነባው ተርሚናሉ፤ ወደ አካባቢው የሚመጡ ቱሪስቶችን ያለምንም መጨናነቅና እንግልት ጥራቱን የጠበቀ አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላል ብለዋል። ይህም በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶችን በስፋት በመሳብ ከተማዋን ይበልጥ ለማዘመን እንደሚያግዝም አስረድተዋል። ተርሚናሉ ደረጃውን ጠብቆ መገንባቱ ለጎብኚዎች ፈጣን አገልግሎት በመስጠት የከተማዋን የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ፍሰቱን ያቀላጥፋል ያሉት ደግሞ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ጋሻው እንዳለው ናቸው።   የተፈጥሮ፣ ሰው ሰራሽና ታሪካዊ ቅርሶች ባለቤት የሆነችውን የባህርዳር ከተማ በኮሪደርና በአረንጓዴ ልማት፣ በሰፋፊ የአስፋልት መንገዶችና በአዲሱ የአባይ ድልድይ ግንባታ በማጀብ ተመራጭ መዳረሻ እንድትሆን መደረጉን አመልክተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው አዲሱ ተርሚናል መንግሥት ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት ማሳያ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ በቀጣይም ዘመናዊ ሎጆችና ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎች ግንባታ ላይ ማተኮር ይገባል ብለዋል።  
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 664 ሺህ 505 አዳዲስ ደንበኞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ ተደርጓል
Aug 7, 2026 460
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 664 ሺህ 505 አዳዲስ ደንበኞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው ገለጹ። የአገልግሎቱ ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው የአገልግሎቱ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅዱ ዙሪያ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ስራ አስፈጻሚው በመግለጫቸው አገልግሎቱ በበጀት ዓመቱ ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑን ጠቁመው፤ በዚህም የደንበኞቹን ቁጥርም 5 ነጥብ 88 ሚሊየን ማድረሱን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ 664 ሺህ 505 አዳዲስ ደንበኞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉንና ከዕቅድ አንጻር 83 ነጥብ 1 በመቶ መከናወኑን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ 205 የገጠር ቀበሌዎችንና መንደሮችን የኤሌክትሪክ ሀይል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም ዋና ስራ አስፈጻሚው ጨምረው አስታውቀዋል። በበጀት ዓመቱ 118 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ለደንበኞች ከቀረበ የኤሌክትሪክ ሀይል ሽያጭ መሰብሰቡንና ከዕቅድ አንጻርም 102 ነጥብ 6 በመቶ ማሳካት መቻሉን አንስተዋል። በኤሌክትሪክ ሀይል ማሰራጫ መስመር መሰረተ ልማት ዝርጋታና ጥገና ላይም ሰፊ ስራ መሰራቱን ጠቁመው በዚህም 4 ሺህ 892 ኪሎ ሜትር ያረጁ የኤሌክትሪክ ማሰራጫ መስመሮች መጠገናቸውን ገልጸዋል። ዋና ስራ አስፈጻሚው አክለውም ከ67 በመቶ በላይ አገልግሎቱ የሚጠቀምባቸው ትራንስፎርመሮች በሀገር ውስጥ የመሚመረቱ መሆናቸውን ጨምረው አስታውቀዋል። ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ለሚገጥሙ የስነምግባር ችግሮች ፈጣንና ተመጣጣኝ እርምጃዎች መውሰዱንና ይህም አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ከአንድ ሚሊየን አንድ መቶ አስራ ሶስት ሺህ አንድ አዳዲስ ደንበኞችን ለማፍራት እንዲሁም 317 የገጠር መንደሮች አዲስ ኀይል እንዲያገኙ መታቀዱን አስታውቀዋል። ከመሰረተ ልማት ማስፋፊያና ጥገና አንጻርም በአዲሱ በጀት ዓመት 12 ሺህ 549 ኪሎ ሜትር የኤሌክትሪክ መስመር እንደሚዘረጋም ገልጸዋል። የኤሌክትሪክ መቆራረጥን መቀነስ የሚያስችሉ ሰፋፊ የመሰረተ ልማት ዝርጋታ እና ጥገና ስራዎች በትኩረት ይከናወናሉ ነው ያሉት። አሁን ላይ አገልግሎቱ የሚጠቀምባቸው ከ67 በመቶ በላይ ትራንስፎርመሮች በሀገር ውስጥ እንደሚመረቱም ኢንጂነር ጌቱ ገረመው በመግለጫቸው ተናግረዋል። የኀይል መቆራረጥ ምጣኔን ለመቀነስ በትኩረት እንደሚሰራ ጠቁመው ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ለሚገጥሙ የስነምግባር ችግሮች ፈጣንና ተመጣጣኝ እርምጃዎች መውሰዱን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።    
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአርሶ አደሮችን ምርታማነት አሳድጓል
Aug 7, 2026 310
‎አለታ ወንዶ ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ያለፉት ዓመታት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ተግባራት ምርታማነታቸው እንዲጨምር ማድረጉን በደቡባዊ ሲዳማ ዞን የአለታ ወንዶ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ በወረዳው የዊቾ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ታፈሰ ዩጤ፤ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በየዓመቱ በግል ማሳቸውና በአካባቢው የወል መሬቶች ላይ ተከላ ሲያከናውኑ መቆየታቸውን ተናግረዋል። በዚህም በአካባቢያቸው ተራቁተው የነበሩ ቦታዎች ለምልመው ወደ አረንጓዴነት መቀየራቸውን ጠቁመዋል። በመርሃ ግብሩ የተከሏቸው የአቮካዶ፣ የማንጎ፣ የሙዝና ሌሎች ፍራፍሬዎች አሁን ላይ ለምርት በመድረሳቸው ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ገልጸዋል። የጎዋዳሞ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ካሰች ዳንሳሞ በበኩላቸው፤ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተከሏቸውን የፍራፍሬና የጥላ ችግኞች በመንከባከብ ለፍሬ እንዲበቁ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። ችግኞቹ አድገው ለቡና ማሳቸው ጥላ ከመሆናቸውም በላይ፣ ፍራፍሬዎቹ ከምግብ ፍጆታ ባለፈ የገቢ ምንጫቸውን ለማሳደግ እንዳስቻላቸው አስረድተዋል። የተሻሻሉ የአቮካዶ ዝርያዎችን በስፋት በማልማት ምርቱን ለኢንዱስትሪና ለሌሎች ገበያዎች እያቀረበ ተጠቃሚ መሆኑን ያነሳው ደግሞ የዶቤ ሰዴቃ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ወጣት ቹቹ ቢረጋ ነው። በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብርም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን የፍራፍሬ ችግኞች በመትከል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ተናግሯል። የደቡባዊ ሲዳማ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ደበበ ሻላ፤ በዞኑ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአካባቢ ሥነ-ምህዳር መጠበቁንና የአርሶ አደሩ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማደጉን ገልጸዋል። በዚም ለደንና ለምግብ የሚሆኑ ችግኞች መተከላቸውን በማንሳት፤ የአፈር ለምነትን ለመጠበቅና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ማስቻሉን ጠቅሰዋል። ለአብነትም በመርሃ ግብሩ ከተተከሉ ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኞች መካከል የቡና ምርታማነት በአማካይ ከ8 ነጥብ 5 ወደ 9 ነጥብ 2 ማደጉን ተናግረዋል። በፍራፍሬ ምርትም አርሶ አደሮች በማኅበር በመደራጀት ምርታቸውን ለይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርት ኢንዱስትሪ ፓርክና ለአዲስ አበባ ገበያ እያቀረቡ ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኙም አስረድተዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ለአሪ ዞን አርሶ አደሮች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እየሆነ ነው
Aug 7, 2026 291
ጂንካ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ለአካባቢ ጥበቃ ካለው ፋይዳ ባሻገር ተጨማሪ የገቢ ምንጭ በመሆን ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአሪ ዞን አርሶ አደሮች ገለፁ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አሪ ዞን ደቡብ አሪ ወረዳ የጎምር ቀበሌ አርሶ አደር ታደሰ ሸዋዬ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ አካባቢያቸው ተራራማና ተዳፋት በመሆኑ በተደጋጋሚ ለአፈር መሸርሸርና ለጎርፍ አደጋ ሲጋለጡ ቆይተዋል። ባለፉት ዓመታት መንግስት የአካባቢውን አርሶ አደሮች በማሳተፍ በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የአፈር መሸርሸርና ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭነታቸው እየቀነሰ መምጣቱን ገልጸዋል።   የተፋሰስ ልማት በተከናወነባቸው አካባቢዎች ፍራፍሬ በማልማት በአሁኑ ወቅት ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ችግኝ በስፋት መትከል ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በአካባቢያቸው ተጨባጭ ለውጦች መታየታቸውን የገለጹት ደግሞ አርሶ አደር ገዛህኝ ገሚጋንሶ ናቸው። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር በተከናወኑ ተግባራት ያገኘነውን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በመገንዘብ ዘንድሮም ልማቱን አጠናክረን ቀጥለናል ያሉት አርሶ አደሩ፣ ልማቱ ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን ተናግረዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ሙዝ፣ አቮካዶ እና ቡና ተክለው በማልማት ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ጠቁመው፣ ይህን ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በየዓመቱ በመርሀግብሩ የሚያደርጉትን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። አካባቢው በስፋት ቡና አብቃይ በመሆኑ ለእርሻ ሥራ ምቹ ባልሆኑ አካባቢዎች ጭምር ቡና ተክለው እያለሙ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ ሌላው የቀበሌው አርሶ አደር ነሽራይ ከራልቆ ናቸው።   ባለፉት ዓመታት የተከሏቸው የቡና ችግኞች ምርት መስጠት እንደጀመሩ ጠቅሰው፣ ቡና ካስገኘላቸው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ አንጻር በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብርም በስፋት መትከላቸውን ተናግረዋል። ቀደም ሲል በአካባቢው በተራቆቱ አካባቢዎች የደን ችግኞችን ብቻ የማልማት ልምድ እንደነበር ያስታወሱት ደግሞ አርሶ አደር ማርታ ማቲዮስ ናቸው። ለደን ልማት ብቻ የሚያገለግሉ ችግኞች ጥቅማቸው ውስን በመሆኑ አሁን ላይ ለምግብነት፣ ለአካባቢ ጥበቃ እና ለገቢ ምንጭነት የሚውሉ ችግኞችን ጭምር በማልማት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። የአሪ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ጉራልቅ ይዥማልቅ በበኩላቸው እንዳሉት የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብርን ተከትሎ በዞኑ እንደ ፓፓያ፣ አቮካዶ፣ ማንጎ እና አፕል ያሉ ፍራፍሬዎች በስፋት እየለሙ ይገኛሉ።   ይህም የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ካለው ፋይዳ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን እያሳደገው መምጣቱን ተናግረዋል። የሀገር በቀል ዛፎች እንደ ኮሶ፣ ዋንዛ፣ ጽድ እና ዝግባ ያሉና ሥነ-ምኅዳርን ለመጠበቅ የሚያስችሉ ችግኞች በተራቆቱ ተራራማ አካባቢዎች በስፋት እየተተከሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል። የአካባቢ ጥበቃ ሥራውን ከዘመናዊ የንብ ማነብ ሥራ ጋር በማስተሳሰር አርሶ አደሮች በዘርፉ ተሰማርተው ገቢያቸውን እንዲያሳድጉ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም አቶ ጉራልቅ አስታውቀዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያረጋገጠ ነው
Aug 7, 2026 274
አርባምንጭ ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት መርሃ ግብር የአካባቢያችንን ሥነ-ምህዳር በማስተካከል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያረጋገጠ ነው ሲሉ የጋሞ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የጋጮ ባባ ወረዳ የጋጼ ቀበሌ ነዋሪዎች አርሶ አደር አልቤ አለሙ እና አርሶ አደር አቡሽ አማሮ፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ለሰብል ምርትና ለእንስሳት መኖ ልማት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል። መርሃ ግብሩ የደን ዛፎችን በመትከል ገላጣ የነበሩ ተራሮች እንዲለሙ ማደረጉን ጠቁመው፤ የአቮካዶ፣ የማንጎ እና የአፕል ፍራፍሬ ችግኞችን በማልማት የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደግ ማስቻሉን ገልጸዋል።   የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የደን ሽፋን እንዲጨምር በማድረጉ በንብ ማነብ ሥራ ተሰማርተው ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ በምዕራብ አባያ ወረዳ የ«ጦይሎ» ንብ አናቢ ማኅበር ሰብሳቢ አቶ ደሴ ኡታሎ ናቸው። ማኅበሩ በ52 አባላት በ2014 ዓ.ም መመስረቱን የጠቀሱት ሰብሳቢው፤ አሁን ላይ በ19 ሄክታር ደን ውስጥ ንብ ከማነብ ባለፈ የደን ጥበቃ ሥራ እያከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል።   የሚያመርቱትንም ማር ለአካባቢው ገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ገቢ በማግኘታቸው አባላቱ በከተማ መኖሪያ ቤት መገንባታቸውንና የሸቀጥ ሱቆችን መክፈታቸውን ገልጸዋል። የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ማጌሶ ማሾሌ በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥና ኢኮኖሚያዊ አቅምን በማሳደግ ረገድ ጉልህ ድርሻ እያበረከተ መሆኑን አስረድተዋል።   መርሃ ግብሩ የዞኑን የደን ሽፋን በማሳደግ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገሩ የልማት ስራዎች እንዲተገበሩ፣ እንዲሁም የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ በማድረጉ የከርሰ ምድር ውሃ መጠንና የአፈር ለምነት እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል። በዚህም ምርትና ምርታማነት ከመጨመሩም ባሻገር አርሶ አደሩ በንብ ማነብ ሥራ ተሰማርቶ ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻሉን አክለዋል። በተጨማሪም በዞኑ የሚገኙ ተራሮች እየለሙ በመምጣታቸው በአባያና ጫሞ ሀይቆች ህልውና ላይ አደጋ እያስከተለ የነበረው የደለል አፈር በእጅጉ መቀነሱን አቶ ማጌሶ ገልጸዋል።
አገልግሎቱ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ውጤታማ ተግባራትን አከናውኗል
Aug 7, 2026 297
አዲስ አበባ፤ ነሃሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑን አስታወቀ። አገልግሎቱ የ2018 በጀት ዓመት በኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት እና የፋይናንስ አፈጻጸሙን እንዲሁም በ2019 በጀት ዓመት ዕቅዱ ዙሪያ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥቷል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው፤ አገልግሎቱ በበጀት ዓመቱ ውጤታማ ተግባራትን አከናውኗል ብለዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ በተከናወኑ በርካታ ተግባራት የደንበኞቹን ቁጥር 5 ነጥብ 88 ሚሊየን ማድረስ መቻሉን ገልጸዋል። ከደንበኞች አገልግሎት አንጻር በቅድመ ክፍያ 82 ነጥብ 6 እንዲሁም በድህረ ክፍያ 15 ነጥብ 4 በመቶ መድረሱንም አክለዋል። በበጀት ዓመቱ 664 ሺህ 505 አዳዲስ ደንበኞች የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን ገልጸው፤ ይህም ከዕቅዱ አንጻር 83 ነጥብ 1 በመቶ መከናወኑን ተናግረዋል። አገልግሎቱ በበጀት ዓመቱ 118 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ለደንበኞች ከቀረበ የኤሌክትሪክ ሀይል ሽያጭ መሰብሰቡን ተናግረዋል። በኤሌክትሪክ ሀይል ማሰራጫ መስመር መሰረተ ልማት ዝርጋታና ጥገና ላይም ሰፊ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል። በዚህም ያረጁ የማሰራጫ መስመሮችን ከመጠገን አንጻርም በበጀት ዓመቱ 4 ሺህ 892 ኪሎ ሜትር የኤሌክትሪክ መስመሮች ላይ የጥገና ስራ ተሰርቷል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መሪነት የአፍሪካ ኃያል ሀገር እየሆነች ነው-ታዋቂው የህንድ ሚዲያ ፈርስት ፖስት
Aug 7, 2026 364
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 1/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) መሪነት የመጪው ዘመን የአፍሪካ ኃያል ሀገር ወደመሆን እየተሸጋገረች ነው ሲል ታዋቂው የህንድ ሚዲያ ፈርስት ፖስት ዘግቧል። ፈርስት ፖስት ሚዲያ ኢትዮጵያን በተመለከተ በሠራው ትንታኔው የሰው ዘር መገኛ፣የጥንታዊ መንግስታት ምድር፣የንግድ መስመሮች እና ከፍ ያለ የአፍሪካ ታሪካዊ መሰረት ያላት ሀገር መሆኗን አውስቷል። ሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ወደ ስልጣን ከመጡ ወዲህ ከቀድሞ ገናና ታሪኳ እኩል ታላቅ የሆነ አዲስ ምዕራፍ ለመገንባት በትጋት ላይ መሆኗን አንስቷል። በጠቅላይ ሚኒስትሩ መሪነት በቀጣናው እና የአፍሪካ ኃያል ሀገር መሆን የሚያስችላትን እንዲሁም የአህጉሪቱን የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚበይንና የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት እየሠራች መሆኗንም እንዲሁ። ለረጅም ዓመታት ዓለም ኢትዮጵያን የሚያውቃት በጦርነት፣በድርቅ እና በፖለቲካዊ አለመረጋጋት እንደነበር በማስታወስ፥ዛሬ ግን ሀገሪቱ ይህንን የተዛባ ትርክት በኢነርጂ መሠረተ ልማት፣ በአቪየሽን፣ በማዕድን እና በዲጂታል ኢኮኖሚ አስደማሚ ለውጦች ለመቀየር እየሠራች ነው ብሏል። ኢትዮጵያ ፈተናዎችን ተሻግራ እንዴት በአፍሪካ ፈጣን ዕድገት ካላቸው ኢኮኖሚዎች ቀዳሚዋ ሆና ልትቀጥል ቻለች? የሚለውን ጥያቄ በማንሳትም በዝርዝር መልሶቹን ያብራራል። የዚህ ዋና ጥያቄ ዝርዝር ምላሽ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት እየተተገበሩ የሚገኙ የኢትዮጵያን የወደፊት እጣ ፈንታ የሚወስኑ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ላይ ነው ያለው ሲል አንስቷል።   • የመጀመሪያው የኢነርጂ አብዮት እና ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ነው። በዚህ የኢትዮጵያ የለውጥ ጉዞ ጎልቶ የሚነሳው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሲሆን፣ ከ5 ሺህ ሜጋዋት በላይ የማመንጨት አቅም ያለው የአፍሪካ ትልቁ የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ፕሮጀክት መሆኑን ፈርስት ፖስት በዘገባው ጠቅሷል። ሕዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ መሻቶች መሰረት፣የኤሌክትሪክ ኃይል፣ የውጭ ምንዛሬ እና የቀጣናዊ ተጽዕኖ መፍጠሪያ አቅም መሆኑንም አብራርቷል። የሕዳሴ ግድብ ልዩ የሚያደርገው የኢትዮጵያ መንግሥትና ሕዝብ ከዓለም ባንክ ወይም ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም አንድ ሳንቲም ሳይበደር በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደም፣ ላብና ገንዘብ የተገነባ አፍሪካውያን በራሳቸው ህልማቸውን ማሳካት እንደሚችሉ ያሳየነው ብሏል። ለኢትዮጵያውያን ግድቡ ከኮንክሪት እና ከተርባይን በላይ ትርጉም አለው ያለው ይህ የፈርስት ፖስት ዘገባ፥ እጅግ የላቀ እራስን የመቻል እና የኢኮኖሚ ነፃነት ማሳያ ሐውልት መሆኑንም ተንትኗል። ኢትዮጵያ ታዳሽ ኃይልን ለኬንያ፣ ለጂቡቲ እና ለሱዳን በመሸጥ ኤሌክትሪክን ወደ ከፍተኛ ገቢ ማመንጫነት እየቀየረች ከመሆኑም በላይ የመላው ምስራቅ አፍሪካ ቀጣናዊ የትስስር ማዕከል ሆናለች ነው ያለው። • የኢትዮጵያ የዕድገት ምሰሶ አቪዬሽን እና ቀጣናዊ ትስስር ኢነርጂ ብቻውን ኢኮኖሚያዊ አቅምን አይገነባም፤ ይልቁንም ኢነርጂ ኢንዱስትሪን ያነቃቃል፣ ትስስር ዓለም አቀፍ ንግድን ይመግባል ያለው ፈርስት ፖስት፥የአፍሪካ ግዙፉ አየር መንገድ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አሁን ለላቀ የዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ጉዞ መጀመሩን አንስቷል። በ12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ግንባታው እየተፋጠነ የሚገኘው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በየዓመቱ እስከ 110 ሚሊዮን ተጓዦችን እና ወደ 4 ሚሊዮን ቶን የሚጠጋ የዕቃ ጭነት ማስተናገድ አቅም አለው። ሙሉ በሙሉ ግንባታው ሲጠናቀቅም በዓለም አቀፍ ደረጃ ከታላላቅ የአቪዬሽን ማዕከላት አንዱ ይሆናል ብሏል።   ይህ ፕሮጀክት የአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የዲፕሎማሲ መናኸሪያ የሆነችውን አዲስ አበባንና አፍሪካን፣ከሌሎች የዓለም ክፍሎች የሚያስተሳስር ዋና የመተላለፊያ ማዕከል እንደሚሆንም ተገልጿል። ስለዚህ አዲሱ የቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ ለንግድ፣ ለኢንቨስትመንት እና ለቱሪዝም፣ ለዓለም የዲፕሎሲ ትብብር ጉልህ ሚና እንዲያበረክት ታስቦ እየተገነባ ነው ብሏል። • የማዕድን ኢንቨስትመንትና በምግብ ራስን መቻል በሌላ በኩል ከኢትዮጵያ መሬት በታች ላለው የማዕድን ሀብቷ ትኩረት በመስጠት የልማት አብዮት እያካሄደች ስለመሆኑም ተንትኗል። ሀገሪቱ የወርቅና ሌሎች ማዕድናት ማውጫ ሜጋ ፕሮጀክቶችን በማስፋፋት አዳዲስ የውጭ ምንዛሬ ምንጮችን እያፈራች የማዕድን ኢንዱስትሪዋን እያሳደገች ነው። ወርቅ በፍጥነት ከኢትዮጵያ ቀዳሚ የወጪ ንግድ ምርቶች አንዱ በመሆን ለረጅም ጊዜ በግብርና ላይ ብቻ ጥገኛ ሆኖ የቆየውን ኢኮኖሚ ወደ ብዝኃ ዘርፍ እያሸጋገረ ይገኛል። በሌላ በኩል በምግብ ራስን ከመቻል ውጭ የትኛውም ኢኮኖሚያዊ ለውጥ የተሟላ ሊሆን አይችልም ያለው የፈረስት ፖስት ዘገባ፥ ግብርና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት መሆኑን ጠቅሷል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሚመራው መንግሥት ኢትዮጵያ በምግብ ራሷን እንድትችል በጀመረው የለውጥ ጉዞ አስደማሚ ውጤት እያመጣ ነው ብሏል። ከዚሁ ጋር በተያያዘም ከጉባ ብስራቶች አንዱ የሆነውና በሶማሌ ክልል እየተገነባ የሚገኘው የማዳበሪያ ፋብሪካ ፕሮጀክት በየዓመቱ 3 ሚሊዮን ቶን የሚጠጋ ዩሪያ ማዳበሪያ ማምረት የሚችል ነው። ይህም ከውጭ የሚገባውን ማዳበሪያ ጥገኝነት በመቀነስ የኢትዮጵያን የግብርና ምርታማነት ለማሳደግ እንደሚያስችል አብራርቷል። "የምግብ ዋስትና የእኛ ስትራቴጂካዊ ጣልቃ ገብነት ነው።ያንን ግብ እውን ለማድረግ ግብአቶች ላይ መስራት አለብን።በግብአት ላይ መስራት ካልተቻለ የምግብ ዋስትናን እውን ለማድረግ መንገድ የለውም" የሚለውን የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ በማካተት ዘገባው ሰፊ ሽፋን ሰጥቷል። ዲጂታላይዜሽን እና የኢንቨትመንትና የገበያ ማሻሻያዎች በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለው ለውጥ ወደ ዲጂታልም እየተሸጋገረ ነው።ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እንደተናገሩት የ5 ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ስልጠና ከዕቅዱ ቀድም ከመሳካቱም በላይ በርካታ ወጣቶች የዲጂታል እውቀት ባለቤት አድርጓል።   በተመሳሳይ የዲጂታል ትስስር እየሰፋ ሲሆን የ4ጂ እና 5ጂ አገልግሎቶች በበርካታ ከተሞች ተደራሽ ሆኗል። ኢትዮጵያ ለበርካታ አስርት ዓመታት ተዘግተው የቆዩ እንደ ቴሌኮሙኒኬሽን፣ ባንክ እና የካፒታል ገበያዎች ያሉ ዘርፎችን ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት ማድረጓንም አድንቋል። የካፒታል ገበያን መጀመሯም የግል ካፒታል ልውውጥን በማጎልበት ለኢኮኖሚ ዕድገት ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ተንትኗል። እነዚህ ማሻሻያዎች በአጠቃላይ በመንግስት ቁጥጥር ስር ከነበረው የኢኮኖሚ ወደ ግል ዘርፍ ኢንቨስትመንት እያደገ የሚሄድ ኢኮኖሚ መሰረታዊ ለውጥን እየተገነባ መሆኑን ያሳያሉ ነው ያለው። ኢትዮጵያ ካላት የጂኦ ፖለቲካ ስትራቴጂካዊ አቀማመጥ አኳያ እድልና ፈተናዎች ከፊቷ መሆናቸውን በማንሳት፥ አዲሱን የዓለም አቀፍ የትብብር ጥምረት ብሪክስ አባል መሆኗን አውስቷል። ከቻይና፣ ከመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት፣ ከምዕራባውያን አጋሮችና ከአፍሪካ ኢንቨስተሮች ኢንቨስትመንትን እየሳበች እንደምትገኝም እንዲሁ። ኢትዮጵያ ጎራ ሳትለይ ከሁሉም የዓለም ሀገራት ጋር ትብብሯን እያጠናከረች ነው ብሏል። ዓለም ኢትዮጵያን የምታስታውሰው በጦርነት ቢሆንም፥ኢትዮጵያ ዓለም በአዲሱ የለውጥና የስኬት ጉዞዋ እንዲያስታውሳት እየሠራች ነው። ለዚህም በመላው ሀገሪቱ በሁሉም ዘርፍ ግዙፍ የኢኮኖሚ ሽግግር እየተካሄደ ሲሆን፥ ይህ የኢትዮጵያ ጉዞ ለቀጣዮቹ ዓመታት የቀጣናውንና የአፍሪካን ኢኮኖሚያዊና አጠቃላይ ገጽታ በአዲስ መልኩ የሚቀርጽ ነው ሲል ፈርስት ፖስት ዘገባውን አብራርቷል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም