ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የመዲናዋ የአመራር አባላት በቁርጠኝነት ሊተጉ ይገባል
Aug 31, 2026 189
አዲስ አበባ ፣ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የመዲናዋ የአመራር አባላት በቁርጠኝነት ሊተጉ እንደሚገባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት እና በ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ዙሪያ ላለፉት ሁለት ቀናት ሲያካሂድ የነበረውን ውይይት አጠናቋል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በውይይቱ ማጠቃለያ ባስተላለፉት የሥራ መመሪያ፤ መዲናዋን የብልጽግና ተምሳሌት የሚያደርጉ ተጨባጭ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቶችን በጥራት፣ በፍጥነትና በተሻለ አቅም የመፈጸም ልምድ እየጎለበተ መሆኑን ገልጸው፤ በውጤታማ የሀብት አጠቃቀም የተመደበው ገንዘብ ለታለመለት ዓላማ በማዋል የተሻለ አፈፃፀም ተመዝግቧል ብለዋል። የሙሉ ቀን ሥራ ባህል እየሆነ መምጣቱን በማንሳት፤ ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመለወጥ ዜጎቸን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥል ገልጸዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር ገቢራዊ በማድረግ በመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚስተዋለውን የመልካም አስተዳደር ችግር በዘላቂነት መፍታት የሚያስችል ውጤት ተገኝቷል ብለዋል። በንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት፣ በመንገድ፣ በጤና፣ ትምህርት፣ የስራ ዕድል ፈጠራ፣ በወንዝ ዳርቻዎችና ኮሪደር ልማት ህዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሥራዎቸን ለማከናወን ዕቅድ መያዙን ገልጸዋል። በመሆኑም አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የመዲናዋ የአመራር አባላት በቁርጠኝነት ሊተጉ ይገባል ብለዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ እና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ጃንጥራር ዓባይ በበኩላቸው፤ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተያዙ ዕቅዶችን ለማሳካት የአመራር አባላት የጋራ ግንዛቤ በመያዝ የለውጥ ርምጃዎችን መጀመር እንዳለባቸው ገልጸዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ዲሞክራሲ ስርዓት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ እንዳሉት፣ህዝቡ በምርጫው የሰጠንን ተጨማሪ ዕድል በልማት ለመካስ ለቀጣይ ተልዕኮ ራሳችንን ማዘጋጀት ይገባናል ብለዋል።
በአማራ ክልል ከአምስት ነጥብ ስድስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ተሸፍኗል
Aug 31, 2026 87
ባህርዳር፣ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ) ፡-በአማራ ክልል በተያዘው የመኸር ወቅት የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ከአምስት ነጥብ ስድስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መሸፈን መቻሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። የቢሮው የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማደፍሮ አስላከ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በ2018/19 የምርት ዘመን በምግብ ራስን ከመቻል ያለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት እየተሰራ ነው። በምርት ዘመኑ ከአምስት ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት የእንክብካቤ ስራ ማከናወን እየተካሄደ እንደሚገኝ ገልጸዋል። አጠቃላይ ከለማው መሬት ውስጥ ከአንድ ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በዘመናዊ ትራክተር በማረስ ማልማት መቻሉንም አመልክተዋል። ከሶስት ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ሄክታር በላይ የሚሆነውን መሬት ደግሞ በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ የለማ መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩ ሰብሉን የማረም፣ የመኮትኮትና ከተባይና ከበሽታ በመከላከል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ለዚህ የምርት ዘመንም አምስት ሚሊዮን ኩንታል የሚጠጋ ዘመናዊ የአፈር ማዳበሪያን ጨምሮ 524 ሺህ ኩንታል የተለያየ ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ መዋሉን አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅት ያለው አፈጻጸም በምርት ዘመኑ ይገኛል ተብሎ የታቀደውን ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ አጠቃላይ ምርት ለማሳካት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የወንበርማ ወረዳ አርሶ አደር ቸኮል ታደለ፤ አራት ሄክታር መሬታቸውን በኩታ ገጠም አስተራረስና በትራክተር በማረስ በቆሎና ስንዴ መዝራታቸውን ገልጸዋል። በባለሙያዎች ምክረ ሃሳብ በመታገዝ የማዳበሪያና የምርጥ ዘር ግብዓት ተጠቅመው ያለሙት ሰብል እድገቱና ቁመናው በተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ከሁለት ሄክታር በላይ መሬታቸውን በወቅቱ በዘር ሸፍነው እየተንከባከቡ እንደሚገኙ የገለጹት ደግሞ በሰሜን ጎጃም ዞን የጎንጅ ቆለላ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አለምነው ደሴ ናቸው። እያለሙት ያለው ጤፍና የበቆሎ ሰብል በጥሩ ቁመና ላይ የሚገኝ በመሆኑ የተሻለ ምርት አገኛለሁ ብለው እየሰሩ መሆናቸውን ነው የጠቀሱት። በ2017/2018 የምርት ዘመን በክልሉ ከለማው አምስት ነጥብ አምስት ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ከ188 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ማምረት መቻሉን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ሕብረተሰቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ልምዱን በማሳደግ አምራቹን ማበረታታት አለበት - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Aug 31, 2026 83
ሃዋሳ፤ ነሐሴ 25/2018(ኢዜአ)፡-ሕብረተሰቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ልምዱን በማሳዳግ በአምራች ዘርፍ የተሰማሩ ባለሀብቶችን ማበረታታት እንዳለበት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ አስታወቁ። የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ''የኢትዮጵያን ይግዙ'' በሚል መሪ ሃሳብ በሀዋሳ ከተማ የተዘጋጀውን የንግድ አውደ ርዕይና ባዛር ከፈተዋል። በንግድ አውደ ርዕዩና ባዛሩ የቀረቡ ምርቶችን ተዘዋውረው የተመለከቱ ርዕሰ መስተዳድሩ ህብረተሰቡ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ባህሉን እንዲያሳድግ ጠይቀዋል። የንግድ ሳምንቱ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት የተረጋጋ የግብይት ሥርዓት እንዲፈጠር አጋዥ መሆኑንም ገልጸዋል። ማህበረሰቡ በአምራች ኢንዱስትሪ መስክ የተሰማሩ ባለሀብቶችን ለማገዝና የሀገር ኢኮኖሚን ለመደገፍ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመግዛትና የመጠቀም ልምዱን ማጎልበት እንዳለበት አስገንዝበዋል። የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ሃላፊዋ ወይዘሮ ሰላማዊት መኩሪያ በበኩላቸው እንዳሉት አውደ ርዕይና ባዛሩ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ባህልን በማሳደግ ኢኮኖሚያዊ አቅምን ለማጠናከር ያለመ ነው፡፡ በአውደ ርዕዩና ባዛሩ ላይ ቁጥራቸው 168 የሚሆኑ አምራቾች፣ ነጋዴዎች፣ ዩኒየኖች፣ ላኪዎች፣ አገልግሎት ሰጪዎችና በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ላይ የሚሳተፉ ማህበራት ጭምር መሳተፋቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚህም መጪዎቹን በዓላት ታሳቢ ያደረጉ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ገበያን የማረጋጋት ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አውደ ርዕይና ባዛሩ ዘላቂ የገበያ ትስስር በመፍጠር በኢኮኖሚ እንቅስቃሴው ላይ ከፍተኛ ፋይዳ ያለው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በአውደ ርዕይና ባዛሩ ላይ ምርታቸውን ካቀረቡት መካከል የሲዳማ ዶና ህብረት ሥራ ዩኒየን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ገነነ ልኡልሰገድ የአትክልና ፍራፍሬ ምርቶችን ይዘው መቅረባቸውን ገልጸዋል። ከ5ሺህ በላይ አባላት የሚሰበስቧቸውን ምርቶችን በተሻለ የገበያ አማራጭ በማቅረብ ገበያን ከማረጋጋት ባለፈ የአባላቱን የገቢ አቅም እያሳደጉ መሆኑን ገልጸዋል። "የኢትዮጵያን ይግዙ" የንግድ አውደ ርዕይና ባዛር የገበያ ትስስር የሚፈጥር ምቹ አጋጣሚ በመሆኑ የአካባቢውን ምርት በሚገባ ለማስተዋወቅ እንደሚጠቀሙበት ገልጸዋል። የብራውን ፉድ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ድርጅት ተወካይ አቶ መርዕድ ጋሹ የንግድ አውደ ርዕይና ባዛሩ ምርቶቻቸውን በማስተዋወቅ የተሻለ የገበያ ትስስር እንደሚፈጥሩበት ገልጸዋል። የንግድ አውደ ርዕዩና ባዘሩ እስከ ጳጉሜን 3 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚቆይ በስነስርዓቱ ላይ ተገልጿል።
ታይላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ስትራቴጂካዊ ግንኙነት ማጠናከር ትፈልጋለች
Aug 31, 2026 209
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ታይላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ስትራቴጂካዊ ትብብር ለማጠናከር እና ከአፍሪካ አህጉር ጋር ያላትን አጋርነት ለማስፋት ፍላጎት እንዳላት የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉአንግኬትኪኦ ገለጹ። የታይላንድ የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉአንግኬትኪኦ በኢትዮጵያ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት አድርገዋል። ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ አዲስ አበባ በደቡብ ምስራቅ እስያ እና በአፍሪካ መካከል ዋና የትስስር ድልድይ ሆና እየወጣች መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ከታይላንድ ጋር የቆየ ታሪካዊ ግንኙነት ያላት ሀገር መሆኗን አንስተው፤ ሀገራቸው ይህንን ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እና ሁለንተናዊ ትብብሯን ለማሳደግ እንደምትሠራ አስታውቀዋል። በተለይም በኢንዱስትሪ ልማት እና በግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመር ረገድ ያላትን መልካም የልማት ተሞክሮ ለኢትዮጵያ ለማካፈል ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል። የጉብኝታቸው ዋና ዓላማም ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ታሪካዊ የሁለትዮሽ ግንኙነት ማጠናከር እና መቀመጫነቱ አዲስ አበባ ከሆነው የአፍሪካ ኅብረት ጋር ያለውን ተሳትፎ ማሳደግ እንደሆነ አብራርተዋል። በዚህም ታይላንድ በአዲስ አበባ ኤምባሲዋን ለመክፈት መወሰኗን ጠቁመዋል፡፡ ሀገራቸው በአፍሪካ ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ተጽዕኖ ለማጠናከር እና አዲስ አበባን የመላው አህጉራዊ ግንኙነቷ ዋና ማዕከል ለማድረግ የምታደርገውን ጥረት የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ሀገራቸው ከአፍሪካ ጋር ያላትን የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ እና የልማት አጋርነት ለማሳደግ ያለመውን "የታይላንድ-አፍሪካ ተነሳሽነት" የተሰኘ መርሃ-ግብር በልዩ ትኩረት እየተገበረች እንደምትገኝ ገልጸዋል። ሚኒስትሩ የአፍሪካ አህጉር ፈጣን ዕድገት በማስመዝገብ ላይ እንደምትገኝ ጠቅሰው፤ አሁን ላይ አፍሪካ በዓለም አቀፍ ደረጃ በደቡቡ የዓለም ክፍል (Global South) ውስጥ ጠንካራ እና ተጽዕኖ ፈጣሪ ድምፅ ሆና መውጣቷን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የደቡቡ የዓለም ክፍል በዓለም አቀፍ መድረክ ያለው ተጽዕኖ እንደሚያመላክት ጠቅሰው፤ የታይላንድ ዋና ዓላማም ከዚሁ እውነታ ጋር የተጣጣመ አህጉራዊ አጋርነት መገንባት መሆኑን ገልጸዋል። ከነባርና ከአዳዲስ የአፍሪካ ሀገራት ጋር በጋራ በመሥራትም ቀደም ሲል ከተመዘገቡት ስኬቶች በላይ በርካታ የጋራ ውጤቶችን ማስመዝገብ እንደሚቻል እምነታቸውን ተናግረዋል። አዲስ አበባ የአሴአን (ASEAN) እና የአፍሪካ ዋና የትስስር ማዕከል መሆኗን የጠቆሙት ዲፕሎማቱ፤ ኢትዮጵያና ታይላንድ በአፍሪካ ኅብረትና በአሴአን መካከል ጠንካራ የትብብር ድልድይ በመገንባት ከፍተኛ ሚና መጫወት እንደሚችሉ ገልጸዋል። በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በከፍተኛ አመራሮች ደረጃ የሚደረጉ የጋራ ጉብኝቶችና ተደጋጋሚ ውይይቶች ወሳኝ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ሚኒስትሩ ታይላንድ እና የአፍሪካ ሀገራት ሕግን መሠረት ያደረገውን ዓለም አቀፍ ሥርዓት ለማስጠበቅ፣ ነፃ ንግድን ለማስቀጠል እና በዓለም የንግድ ድርጅት (WTO) ሥር ያለውን የንግድ ሥርዓት ለማጠናከር በጋራ መሥራት እንዳለባቸው አሳስበዋል። የኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል መሆንም ከዓለም አቀፍ የንግድ ሕጎች እና ኢኮኖሚ ጋር በንቃት እንድትሳተፍ የሚያበረታታ መሆኑን አብራርተዋል።
በክልሉ በመንገድና ትራንስፖርት ልማት ዘርፍ የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ አበረታች ሥራዎች ተከናውነዋል
Aug 31, 2026 78
ወልቂጤ፣ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ):-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በመንገድና ትራንስፖርት ልማት ዘርፍ የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ አበረታችሥራዎች መከናወናቸውን የክልሉ መንገድና ትራንስፖርት ልማት ቢሮ አስታወቀ። ከክልሉ፣ ከዞኖችና እና ልዩ ወረዳ የመጡ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በትራንስፖርትና መንገድ ልማት ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ ዛሬ በወልቂጤ ከተማ ተካሂዷል። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የመሰረተ ልማት ክላስተር አስተባባሪ እና የትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ሃላፊ መሀመድ ኑርዬ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ለትራንስፖርት እና ለመንገድ ልማት ሥራዎች በተሰጠ ትኩረት ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረገ አበረታች ውጤት ተገኝቷል። በተለይ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዘርፉ የክልሉን ህዝብ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተከናወኑ ሥራዎች በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸውን ነው ያመለከቱት። በዘርፉ የተከናወኑ እነዚህ ተግባራት የሕዝብን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ከማቀላጠፍ ባለፈ ለክልሉ ሁለንተናዊ ዕድገት መጠናከር ወሳኝ ሚና እንዳላቸውም አስረድተዋል። በመናኸሪያዎች የኢ-ትኬቲንግ አሰራርና ሌሎች የሪፎርም ሥርአቶችን ከመዘርጋት ባለፈ በትራንስፖርት አገልግሎት ላይ ጠንካራ ቁጥጥርና የህግ ማስከበር ሥራ መሰራቱ ለውጥ አምጥቷል ብለዋል። እንደ ቢሮ ሀላፊው ገለጻ በክልሉ የትራንስፖርት አቅርቦት እጥረት በነበረባቸው አካባቢዎች አዳዲስ የሕዝብ ትራንስፖርት ስምሪቶችን በማስጀመር የኅብረተሰቡን ጥያቄዎች ለመመለስ ተችሏል። የተቀናጀ የትራንስፖርት አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሠራሮች በመዘርጋታቸውም የትራፊክ አደጋን መቀነስ አስችሏል ብለዋል። እንደ መሀመድ (ዶ/ር) ገለጻ በመንገድ መሰረተ ልማት አዳዲስ የመንገድ ፕሮጀክቶችን ከመገንባት ባለፈ የነበሩትን በመጠገንና ደረጃቸውን በማሻሻል የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በመንግስትና በህብረተሰቡ ተሳትፎ 52 የመንገድ ፕሮጀክቶች ለመገንባት መቻሉን ነው የገለጹት። መንግስት አርሶ አደሩን፣ ባለሀብቱንና የአካባቢውን ተወላጆች በማስተባበር የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያከናውናቸው ተግባራት በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በብልጽግና ፓርቲ የጉራጌ ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ናስር ሃሰን በበኩላቸው እንዳሉት በዞኑ በህብረተሰብ ተሳትፎ የመንገድ ከፈታና የድልድይ ግንባታ ፕሮጀክት ሥራዎች ተከናውነዋል። ለአገልግሎት የበቁት እነዚህ ፕሮጀክቶች ለዓመታት ከህዝብ ሲነሱ የነበሩ ቅሬታና የልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ ማስቻላቸውን ተናግረዋል። በመደመር መንግስት ህዝብን በማሳተፍ የሚሰሩ የልማት ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።
በጋምቤላ ክልል ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ኢንሼቲቭን ስኬታማ ለማድረግ የባለድርሻ አካላት አስተዋጾ እንዲጠናከር ተጠየቀ
Aug 31, 2026 100
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 25/ 2018 (ኢዜአ)፡-በጋምቤላ ክልል ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ኢንሼቲቭን ስኬታማ ለማድረግ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎና ትብብር ሊጠናከር እንደሚገባ ተገለፀ። በብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ላይ ያተኮረ እና የዘርፉ ተመራማሪዎችና ባለሙያዎች የተሳተፉበት የውይይት መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተካሂዷል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አድሮው ቱት በውይይት መድረኩ ላይ እንዳሉት መንግስት የግብርናን ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል። በተለይም የፍራፍሬ ልማት በገበያ ተፈላጊነቱ እየጨመረ መምጣቱን ጠቅሰው፣ ይህም የአርሶ አደሮችን ገቢ በማሳደግ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። እንደ ሀገር ተግባራዊ መደረግ የጀመረው ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም ኢኒሼቲቭ በፍራፍሬ ልማት ዘርፍ የታለመውን ግብ ለማሳካት አበርክቶው የላቀ ነው ብለዋል። ኢኒሼቲቩ በክልሉም ተግባራዊ መደረግ መጀመሩን ገልጸው፣ ስኬታማ እንዲሆንም የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ወሳኝ ሚና እንዳለው ገልፀዋል። በክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ የብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ አብርሃም ኡቻላ በበኩላቸው በክልሉ ለአቮካዶ ልማት ምቹ ስነ-ምህዳር ባላቸው የጎደሬና የመንገሺ ወረዳዎች ብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም መጀመሩን ተናግረዋል። በነዚሁ ወረዳዎች የአቮካዶ ልማቱን በማስፋትና ለአርሶ አደሩ በማስተዋወቅ ምርታማቱን እንዲያሳድግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። መድረኩ በአቮካዶ ችግኝ ልማትና የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎችን ማጠናከር፣ የአቮካዶ የድህረ ምርት አያያዝና የገበያ ትስስርን መፍጠር እንዲሁም የባለሙያዎችና የአርሶ አደሮችን ተሳትፎ ማሳደግ ላይ ያተኮረ መሆኑ ታውቋል።
በሲዳማ ክልል የንግድ ሥርዓቱን ፍትሃዊነትና ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ሥራ ይጠናከራል
Aug 31, 2026 88
ሀዋሳ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የንግድ ስርዓቱን ፍትሃዊነትና ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ስራ እንደሚጠናከር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ከንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ጋር በመተባበር ባዘጋጀው "የኢትዮጵያን ይግዙ" የንግድ ሳምንት ላይ ያተኮረ ውይይት በሃዋሳ ከተማ እየተካሄደ ነው። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በመድረኩ ላይ እንደተናገሩት በክልሉ የንግድ ስርዓቱን ፍትሃዊነትና ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ሥራ ይጠናከራል። ለዚህም ህጋዊ አሰራሩን የማዘመን ተግባራትን በማስቀጠል ኢኮኖሚያዊ ፋይዳውን ለማጉላት ይሰራል ብለዋል። በንግድ ሥርዓት ውስጥ የሚታየውን ህገወጥነት ከመከላከል ባለፈ ግብር ከፋዩን በማበረታታት በዘርፉ ያሉ ማነቆዎችን ለመፍታት በቅንጅት እንደሚሰራም አመልክተዋል። በዚህም የማምረት አቅምን በማጎልበት በክልሉ ያሉ አስመጪና ላኪዎችን ቁጥር የማሳደግ ሥራ በትኩረት እንደሚከናወን ገልጸዋል። የሲዳማ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሰላማዊት መኩሪያ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በክልሉ የሚካሄደው የንግድ ሳምንት የሀገር ውስጥ ምርት የመጠቀም ልምድን እያሳደገ መጥቷል። በዚህም በኢንዱስትሪና በግብርና ምርት ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎች፣ ዩኒየኖች፣ ማህበራትና ሌሎች የዘርፉ ተዋንያን የተፈጠረላቸውን የግብይት ሥርአት በመጠቀም ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል። በዘንድሮው የንግድ ሳምንት መጪዎቹን በዓላት ታሳቢ ያደረጉ ምርቶችን በማቅረብ ገበያን ከማረጋጋት ባለፈ በክልሉ የኤክስፖርት ምርት ላይ ያተኮረና በጥናት የተደገፈ ውይይት እንደሚካሄድ ገልጸዋል። በዚህም ቡናን ጨምሮ በአቮካዶና በሌሎች የኤክስፖርት ምርቶች ላይ ያለውን አቅም በመለየት የንግድና ግብይት ስርአቱን የማሳለጥ ሥራ በትኩረት ይከናወናል ብለዋል። በመድረኩ በኤክስፖርት ምርት ላይ ያተኮረ ጥናታዊ ጽሁፍ ቀርቦ ውይይት የተደረገበት ሲሆን "የኢትዮጵያን ይግዙ" በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀ የንግድ አውደ ርዕይና ባዛርም ይከፈታል ተብሎ ይጠበቃል።
የማዕድን ሀብትን በዘላቂነት በማልማት እና በአግባቡ በማስተዳደር ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ማሳደግ ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን
Aug 31, 2026 65
አሶሳ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፡- የማዕድን ሀብትን በዘላቂነት ለማልማት እና በአግባቡ ለማስተዳደር የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ በየደረጃው ከሚገኙ የዘርፉ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ጋር የማዕድን ሀብትን በዘላቂነት ማልማት በሚቻልበት መስክ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ አካሂዷል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻደሊ ሀሰን፤ የማዕድን ሀብት የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በመደገፍና የውጭ ምንዛሬ በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በክልሉ የማዕድን ሀብት በስፋት እየተመረተ ቢሆንም ህገ-ወጥ እንቅስቃሴዎችን መቆጣጠርና ዘርፉን በአግባቡ ማስተዳደር እንደሚገባ አሳስበዋል። በአሁኑ ወቅትም የማዕድን ሀብትን በዘላቂነት ለማልማት እና በአግባቡ ለማስተዳደር የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ነው የጠቀሱት። የወጡ ህጎችና አዋጆች በዘርፉ የተሰማሩ አካላትን ተጠቃሚ የሚያደርጉ በመሆናቸው በአግባቡ መተግበር እንዳለባቸው ነው የጠቆሙት። በመሆኑም ማዕድን የሚወጣባቸውን አካባቢዎች መልሶ በማልማት የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የክልሉ ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ቱጃኒ አደም በበኩላቸው፤ በክልሉ የሚገኙ የማዕድን ሀብቶችን ለይቶ በማልማት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የማዕድን ሀብት የግጭት መንስኤ እንዳይሆን የዘርፉ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት በህግ አግባብ ብቻ መንቀሳቀስ እንዳለባቸው አሳስበዋል።
በክልሉ የመሬት ሀብት አስተዳደርን በማዘመን የሕዝብ ተጠቃሚነትን የማረጋገጥ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Aug 31, 2026 83
አርባ ምንጭ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመሬት ሀብት አስተዳደር ሥርዓትን በማዘመን የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ሥራዎች እንደሚጠናከሩ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ፡፡ የክልሉ መሬት አስተዳደር ቢሮ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን በ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና በ2019 ዕቅድ ላይ የሚመክር መድረክ ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ አካሂዷል። በመድረኩ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ እንዳሉት በክልሉ የመሬት አስተዳደር ሥርዓትን በማዘመን የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተቀናጀ ተግባር እየተከናወነ ነው። በዚህም የወል፣ የመንግስትና በተቋማት የተያዙ መሬቶችን ለይቶ በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋልና ከመሬት ጋር ተያይዞ የሚነሱ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ ምዝገባ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። የክልሉ መንግስት የከተማና የገጠር መሬት አስተዳደር ሥርዓትን በማዘመን የዜጎች የመሬት ይዞታ ባለቤትነትን ለማረጋገጥ ባከናወናቸው ተግባራት ውጤት መመዝገቡንም ተናግረዋል፡፡ እንደ እሳቸው ገለጻ የመሬት አስተዳደር ሥርዓቱ በዲጂታል አሠራር በመታገዙ በዘርፉ የሚፈጸሙ ህገ-ወጥነትና የመሬት ወረራን ለመቆጣጠር ምቹ ሁኔታ የፈጠረ ሲሆን፤ የተጀመሩ ሥራዎችም ተጠናክረው ይቀጥላሉ። በክልሉ በ65 ወረዳዎች እየተካሄደ ያለውን የመሬት ምዝገባ በውጤተማነት ለማጠናቀቅ በየደረጃው የሚገኘው አመራርና ባለሙያው የበኩሉን እንዲወጣም አሳስበዋል። የክልሉ መሬት አስተዳደር ቢሮ ሃላፊ ሰብስቤ ቡናቤ በበኩላቸው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ ባሉ ወረዳዎች ቀደም ሲል በማኑዋል የነበረውን የመሬት አስተዳደር ሥርዓት ወደ ሲስተም አሰራር መቀየር ተችሏል ብለዋል። የመሬት ሀብትን በዘመናዊ የመረጃ አያያዝ ሥርዓት በመምራት ፍትሃዊ የመሬት አጠቃቀም ለማስፈንና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ጉባኤው በ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ላይ ከመከረ በኋላ በተያዘው በጀት ዓመት ዕቅድ ላይም ተወያይቶ የጋራ አቅጣጫዎችን ያስቀምጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ባለፉት አምስት ዓመታት በሥራና ክህሎት ዘርፍ ጠንካራ መሠረት ተጥሏል
Aug 31, 2026 84
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በባለፉት አምስት ዓመታት በሥራና ክህሎት ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ለቀጣይ የልማት ጉዞ ጠንካራ መሠረት መጣላቸውን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ካሚል ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ባለፋት አምስት ዓመታት በሥራና ዕድል ፈጠራ በክህሎትና ልማት እንዲሁም የአሠሪና ሠራተኛ ዘርፍ ዋና ዋና የልማት ስኬቶችን ልምዶችንና የወደፊት አቅጣጫዎቸን የሚገመግም የምክክር መድረክ እያካሄደ ይገኛል። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ባለፉት አምስት ዓመታት የቴክኒክና ሙያ ሥልጠናን ከዘመኑ አስተሳሰብና ከገበያ ፍላጎት ጋር ለማጣጣም የሚያስችሉ መሠረታዊ ሥራዎች ተከናውነዋል። በዚህም የኢኮኖሚ ኮሪደሮችና የዞን ክፍፍሎችን መሠረት ያደረገ የሥልጠና ተቋማት አደረጃጀት በማካሄድ ከአካባቢው የኢኮኖሚ ሀብትና ከኢንዱስትሪ ፍላጎት ጋር የተጣጣመ የሰው ኃይል ለማፍራት እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። የኢንዱስትሪ ሰላምን ለማረጋገጥም በአሰሪና ሠራተኛ መካከል ያለውን ግንኙነት የሚያሻሽል ሕጋዊ ማዕቀፍ ከመዘርጋት ባለፈ ማህበራዊ ውይይትን፣ የሥራ ቦታ ደህንነትና ጤንነትን ያማከሉ ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። ለቀጣዩ የልማት ጉዞ የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚው ውስጥ የሚኖረውን ቀዳሚ ሚና ለማጠናከር የሥልጠና ሥርዓቱን ከኢንዱስትሪው ጋር ማጣጣም ዋነኛ ትኩረት መሆኑን አስረድተዋል። በዚህ ረገድ የግሉ ዘርፍ በሥልጠና ዲዛይን፣ አፈጻጸምና ግምገማ ላይ በንቃት እንዲሳተፍ የተጀመረውን 'ሴክተር ስኪል ኢኒሼቲቭ' ወደ ቀጣይ ምዕራፍ ማሸጋገር ያስፈልጋል ብለዋል። የዲጂታል ክህሎት ልማትም የቀጣይ ትኩረት መሆኑን ጠቁመው፤ የዲጂታል 2030 ስትራቴጂን ለማሳካት ዜጎችን በዲጂታል ክህሎት ማስታጠቅ የሚኒስቴሩ ቁልፍ ኃላፊነት መሆኑን ጠቅሰዋል። በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተጀመረውን የ5 ሚሊዮን ኮደሮች ኢኒሼቲቭ ወደ 7 ሚሊዮን ለማሳደግና ከዚያም በላይ ለማስፋት እንደሚሠራ አመልክተዋል። ኢንተርፕረነርሺፕን ማስፋትና የፈጠራ ሥራዎችን ማበረታታትም የቀጣይ አቅጣጫ መሆኑን ሚኒስትሯ ገልጸዋል። የሥልጠና ተቋማትንም ከመንግሥት በጀት ጥገኝነት በማላቀቅ ጥራት ያለው ሥልጠናና የቴክኖሎጂ ሽግግር የሚያካሂዱ እንዲሆኑ ማድረግ ይጠበቃል ብለዋል። የልማት ሁሉ ማዕከል ሰው በመሆኑ የሠራተኛውን ብቃት፣ ተነሳሽነት፣ ክብርና ደህንነት ማረጋገጥም የቀጣይ ሥራዎች ትኩረት እንደሚሆን አስታውቀዋል። የአምስት ዓመቱ ስኬቶች የአንድ ተቋም ብቻ ውጤት ሳይሆኑ የክልል አመራሮች፣ የተጠሪ ተቋማት፣ ሠራተኞች፣ የማህበራዊ አጋር አካላት፣ የፋይናንስ ተቋማትና ሌሎች አጋሮች የጋራ ጥረት ውጤት መሆኑን ገልጸው ለተደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። በመድረኩ የ“Skill Ethiopia” ኤክስፖም ተዘጋጅቶ በሥራና ክህሎት ዘርፍ የተሰማሩ ሥራ ፈጣሪዎችና ባለሙያዎች የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ለማስተዋወቅ ዕድል ተፈጥሯል።
የዘንድሮ የዝናብ ሥርጭት ለግብርናው ምቹ በመሆኑ አስፈላጊውን የሰብል እንክብካቤ እያደረግን ነው -አርሶ አደሮች
Aug 31, 2026 114
ጊምቢ፤ ነሐሴ 25/ 2018 (ኢዜአ)፦ በምእራብ ወለጋ ዞን የዘንድሮው የአየር ንብረት እና የዝናብ ስርጭት ለእርሻው ምቹ በመሆኑ አርሶ አደሮች ለሰብላቸው ተገቢውን እንክብካቤ በማድረግ ላይ መሆናቸውን ገለጹ። ምዕራብ ወለጋ ዞን ለም መሬት፣ የተስማማ የአየር ንብረት እና ከፍተኛ የውሃ አማራጭ እንዲሁም የግብርና እምቅ አቅም ካላቸው አካባቢዎች አንዱ ነው። በዞኑ በዋናነት እንደ በቆሎ፣ ጤፍ፣ ማሽላ እና ስንዴ ያሉ የሰብል አይነቶች በሰፊው የሚመረቱ ሲሆን፣ አካባቢው በከፍተኛ የቡና አምራችነቱም ይታወቃል። የዞኑ አርሶ አደሮችም ይኸን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም የእርሻ ስራቸውን በሙሉ አቅም በመተግበር ላይ ይገኛሉ። አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንደገለጹት የዘንድሮው የአየር ንብረት እና የዝናብ ስርጭት ለልማት ስራቸው ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩ እና በቂ የግብዓት አቅርቦት በመኖሩም በዘር የሸፈኑትን ሰብላቸውን በመንከባከብ ላይ ይገኛሉ። ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል የጊምቢ ወረዳ አርሶ አደር ፍቃዱ ቃሲም፤ የዘንድሮው የዝናብ ስርጭት ለሰብል ልማት ሥራቸው ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል። በዚህም በአንድ ሄክታር መሬት ላይ በቆሎና ሩዝ ማልማታቸውን የገለጹት አርሶ አደሩ፣ የአየር ንብረቱ ለሰብሉ አስፈላጊውን እንክብካቤ ለማድረግ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል። የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ኤባ ኦልጂራ በበኩላቸው፣ አንድ ሄክታር ተኩል መሬት በበቆሎና በስንዴ ሰብል ማልማታቸውን ገልጸዋል። የግብርና ግብዓቶች በወቅቱ ስለቀረቡላቸው አስቀድመው በዘር የሸፈኑትን መሬት፣ አሁን እየጣለ ባለው ምቹ የዝናብ ሁኔታ ታግዘው አስፈላጊውን እንክብካቤ በማድረግ ላይ እንደሚገኙ አመልክተዋል። የዘንድሮው የመኸር ወቅት ለሰብል ልማት ሥራ ምቹ በመሆኑ፣ የዘር ሥራቸውን በወቅቱ አጠናቀው እንክብካቤውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ እያገዛቸው መሆኑን የገለጹት ደግሞ የላሎ አሳቢ ወረዳ አርሶ አደር ፋረዳ ኦሊቃ ናቸው። በዚህም የተሻለ ምርት ለማግኘት ከግብርና ባለሙያዎች የሚያገኙትን ምክር በአግባቡ በመተግበር ጠንክረው እንደሚሰሩ ተናግረዋል። የምዕራብ ወለጋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፈይሳ ሐምቢሳ በበኩላቸው፤ በዘንድሮው የመኸር ወቅት በዞኑ 486ሺህ 836 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር መሸፈኑን ገልጸዋል። ልማቱ በአብዛኛው በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ በዘር መሸፈኑን ጠቁመው፤ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስፈልጉ የተለያዩ የግብርና ግብዓቶችም በወቅቱ ለአርሶ አደሩ መቅረባቸውን ኃላፊው አንስተዋል። በአጠቃላይ በዞኑ በተያዘው የመኸር እርሻ መርሃ ግብር ከ16 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል።"
የአዲስ አበባን የአምስት ዓመታት ስትራቴጂክ ዕቅዶች በሚገባ በመተግበር የነዋሪዎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት ይሰራል – የከተማ አስተዳደሩ ሥራ ኃላፊዎች
Aug 31, 2026 104
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባን የቀጣይ አምስት ዓመታት ስትራቴጂክ ዕቅዶች በሚገባ በመተግበር የነዋሪዎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እንደሚሰራ የከተማ አስተዳሩ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቀጣይ አምስት ዓመትና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ በየደረጃው ባሉ የከተማ አስተዳደሩ የሥራ ኃላፊዎች ውይይት ተደርጎበት ዛሬ ይጠናቀቃል። በአምስት ዓመቱ ዕቅድ በከተማ ግብርና፣ በቤቶች ግንባታ፣ በመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥ፣ በቴክኖሎጂ እንዲሁም በሌሎች ሰው ተኮር ሥራዎች የመዲናዋን ሁለንተናዊ ብልጽግና የሚያረጋግጡ ተግባራት ለማከናወን የሚያስችል የጋራ መግባባት ላይ ይደረሳል። የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተቋማት ያለፈውን የአምስት ዓመት ስትራቴጂያዊ ዕቅድ በሚገባ በመፈጸም ያሳዩትን ቁርጠኝነት በቀጣዮቹ ዓመታትም አጠናክረው እንዲቀጥሉ ግልጽና ሊያሰራ የሚችል ዕቅድ ነድፈው እንዲንቀሳቀሱ የሥራ መመሪያ ሰጥተዋል። የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ለኢዜአ እንዳሉት፤ የአዲስ አበባን የአምስት ዓመታት ስትራቴጂክ ዕቅድ በመተግበር የነዋሪዎችን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ይሰራል። የአዲስ አበባ ከተማ የንግድ ቢሮ ኃላፊ ሀቢባ ሲራጅ እንዳሉት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማፋጠን የንግድ ሥርዓቱን የአገልግሎት ምኅዳር የሚያሳልጥ አሰራር ተዘርግቷል። ከ95 በመቶ በላይ አገልግሎቶችን በዲጂታል እንዲሰጡ በማድረግ ለንግዱ ማኅበረሰብ ቀላልና ምቹ የሥራ ከባቢ ተፈጥሯል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪ ከ2013 ዓ.ም. በኋላ 7 የገበያ ማዕከላትን መገንባታቸውን በመጥቀስ፤ የሰንበት ገበያዎችን ቁጥር ወደ 264 ማድረስ እንደተቻለ ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ቅድስት ወልደጊዮርጊስ በበኩላቸው፤ በመዲናዋ ዜጎችን የቤት ባለቤት ማድረግ የሚያስችሉ ውጤታማ የቤት ልማት ሥራዎች ተከናወነዋል ብለዋል። መንግሥት የግሉን ዘርፍ ጭምር በማሳተፍ ባለፉት አምስት ዓመታት 496 ሺህ የሪል ስቴት ቤቶች እንዲገነቡ ማድረጉን ገልጸዋል። በዚህም መንግሥት የግል አልሚዎች በተለያዩ የግንባታ ዓይነቶች በቤት ልማት ዘርፍ እንዲሰማሩ የሚያስችል ምቹ ምኅዳር ፈጥሯል ብለዋል። የንግድ ቢሮ ኃላፊዋ ሀቢባ ሲራጅ በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የንግዱን ማኅበረሰብ ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ በመፍታት ፍትሐዊ የንግድ ውድድር የሚሰፍንበት አውድ እንደሚፈጠር ገልጸዋል። በአምስት ዓመት ውስጥ 357 የእሁድ ቅዳሜ ገበያዎችን እንዲሁም የግብርና ምርቶችን በጥራት፣ በዓይነትና በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት የሚችሉባቸውን የገበያ ማዕከላት ለመገንባት ዕቅድ ተይዟል ብለዋል። ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ቅድስት ወልደጊዮርጊስ በበኩላቸው፤ በቀጣይ አምስት ዓመታት የመዲናዋን ነዋሪዎች የቤት ፍላጎት ታሳቢ ያደረጉ የቤት ልማት ግቦች መያዛቸውን ገልጸዋል። በዚህም በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ዘመኑ የደረሰባቸውን የግንባታ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም በመንግሥትና በግሉ ዘርፍ አጋርነት በየዓመቱ 100 ሺህ ቤቶች ለመገንባት ታቅዷል ብለዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመኸር እርሻን ውጤታማ ለማድረግ ለግብርና ቴክኖሎጂዎችና ግብዓት ትኩረት ተሰጥቷል
Aug 31, 2026 100
አርባ ምንጭ፤ ነሐሴ 25/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመኸር እርሻን ውጤታማ ለማድረግ ለግብርና ቴክኖሎጂዎችና ለግብዓት አቅርቦት ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፣ በክልሉ በመኸር እርሻ ከ230 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች እየለማ ይገኛል። በመኸር እርሻው የስራስር ተክሎች፣ የጓሮ አትክልት እና ድርቅን መቋቋም የሚችሉ እንደ ካሳቫ እና ማሽላ ያሉ ሰብሎች በስፋት እየለሙ መሆናቸውንም አመልክተዋል ልማቱ በአረምና ተባይ እንዳይጎዳ ክትትል ከማድረግ ባለፈ ዝናብ አጠር በሆኑ አካባቢዎች ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎች መዘራታቸውን ተናግረዋል። በክልሉ ጋሞ ዞን ዲታ ወረዳ አርሶ አደር ኦርዛማ ኡርካ ሦስት ሄክታር መሬታቸውን በስንዴ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል። የስንዴ ልማቱን በኩታ ገጠም ማከናወናቸው የማሳ እንክብካቤና ቁጥጥሩን በጋራ ለማድረግ እንዳስቻላቸው ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅትም ሰብሉ በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዞኑ ዳራማሎ ወረዳ ሉና የተቀናጀ የእርሻ ድርጅት ሥራ አስኪያጅ ደመቀ ቶላ በበኩላቸው በ400 ሄክታር ማሳ ላይ በቆሎና የተለያዩ የጓሮ አትክልቶን እያለሙ መሆናቸውን ተናግረዋል። ምርታማነታቸውን ለማረጋገጥ ማዳበሪያና ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂ እየተጠቀሙ በመሆኑ አዝመራው በጥሩ ቁመና ላይ ይገኛል ብለዋል። ለምርትና ምርታማነት የግብርና ባለሙያዎች ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እያደረጉላቸው መሆኑን ጠቅሰዋል።
የባሕር በር ለአገር ደኅንነትና ዕድገት ወሳኝ በመሆኑ ዘላቂ መፍትሔ ማግኘት አለበት-አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ
Aug 30, 2026 371
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለአገር ደኅንነትና ዕድገት ወሳኝ በመሆኑ በሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገዶች ፈጣንና ዘላቂ መፍትሔ ማግኘት አለበት ሲሉ የቀድሞው የውሃ ሚኒስትር አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ አስታወቁ። አምባሳደር ሽፈራው ጃርሶ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የዓባይ ምንጭ ባለቤት በመሆኗ ግብፅና ታሪካዊ ጠላቶቿ በሸረቡት ሀገርን የማዳከም ሴራ ከቀይ ባሕር እንድትገለል ተደርጓል። ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነቷን ያጣችበት ኢ-ፍትሐዊ ሸፍጥም ሦስት አስርት ዓመታትን ያህል እንደሆነው አስታውሰዋል። ግብፅ የሀገር ውስጥ ባንዳዎችን በመጠቀም ኤርትራ እንድትገነጠል ያደረገችበት ታሪካዊ ክህደት ያወሱት አምባሳደር ሽፈራው፤ በዚህም ኢትዮጵያ ተፈጥሯዊ ሀብቶቿ የሆኑትን አሰብና ምፅዋን እንድታጣ መደረጉን ገልጸዋል። ግብፅና የሀገር ውስጥ ባንዳዎች ኢትዮጵያ ከዓለም የምትገናኝባቸውን የባሕር በር መዳረሻ ወደቦች እንድታጣ አድርገዋል ብለዋል። በሕዝብ ያልተመረጠ መንግሥት ሀገርን በመገንጠል ያለ አንዳች ማስረጃ ኢትዮጵያን ወደብ አልባ የማድረግ ምንም ዓይነት ሥልጣን እንዳልነበረው አስታውሰዋል። በዚህም የሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን የኢትዮጵያን የባሕር መዳረሻ ወደቦች አሳልፎ በመስጠት በሀገርና ሕዝቦቿ ላይ ታሪክ ይቅር የማይለው በደል መፈጸሙን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከታሪካዊ፣ ሕጋዊ፣ ተፈጥሯዊና መልክዓ ምድራዊ የባሕር በር ባለቤትነቷ ርቃ ልትኖር እንደማትችል አመልክተው፤ እየተመዘገበ ያለው ፈጣን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴና የሕዝብ ቁጥሯም አስገዳጅ ነው ብለዋል። የባሕር በር ባለቤትነትንም በሰላማዊ፣ ሰጥቶ መቀበል መርህና ዓለም አቀፍ ሕግጋት ጭምር ምላሽ ማስገኘት እንዳለበት አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅት መንግሥት በሕዝብ ልብ ውስጥ ተዳፍኖ የቆየውን የኢትዮጵያ የባሕር በር አስፈላጊነት የዓለም ሀገራት እንዲገነዘቡት በማስቻል ስኬታማ የዲፕሎማሲ ሥራ እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በቀይ ባህር ቅርብ ርቀት ላይ የምትገኝ መሆኗን ገልጸው ፤ ጥያቄውም ከጥንታዊ የሀገር ሥልጣኔ እስከ ሕግጋትና ተፈጥሯዊ ድረስ ምክንያታዊ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ላይ የተፈጸመው በደል ከምክንያታዊነት ወሳኝ የሕልውና ጉዳይ መሆኑም አስረድተዋል። በቀጣይም በድንበር ተሻጋሪ ወንዞቿ ጎረቤቶቿን ተጠቃሚ የምታደረገው ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነቷም ምላሽ ሊያገኝ የሚገባ የትውልድ ጥያቄ መሆኑን አንስተዋል።
በሐረሪ ክልል በመደመር መንግሥት ዕይታ የግብርናው ዘርፍ ምርትና ምርታማነት እመርታዊ ለውጥ
Aug 30, 2026 121
በሐረሪ ክልል በመደመር መንግሥት ዕይታ በግብርናው ዘርፍ ምርትና ምርታማነት እመርታዊ ለውጥ ተመዝግቧል። በመደመር መንግሥት ዕይታ በግብርናው ዘርፍ ገበያ ተኮር ምርቶችን በዓይነት፣ በምርት ብዛትና በጥራት የማምረት እመርታዊ ለውጥ መመዝገቡን ተችሏል። በዚህም የተቀናጀ የግብርና ስራ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ተጨባጭ ስኬቶች ተመዝግበዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት በሰብል፣በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በእንስሳት ሀብት ልማት፣ በሌማት ትሩፋትና በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ላይ ውጤታማ ስራዎች ተከናውነዋል። በክልሉ ከተማና ገጠር ወረዳዎች በሌማት ትሩፋት መርሃግብር የእንስሳት ተዋጽኦና የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት አበረታች ስራዎች ተሰርቷል። በተለይም በገጠር ወረዳዎች በመስኖ ልማት የተከናወኑ ስራዎች ምርትና ምርታማነት እንዲጎለብትና የአርሶ አደሩ የምግብ ዋስትና እንዲረጋገጥ ከማስቻል ባለፈ ለገበያ አቅርቦት ከፍተኛ እገዛ እያደረጉ ይገኛሉ። በሰብል ልማት በየተከናወኑ ተግባራትም አርሶ አደሩን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት እያሸጋገሩ የሚገኙ ውጤት መመዝገብ ተችሏል። በተለይም በክልሉ የዝናብ እጥረትና በሽታን በመቋቋም በአጭር ጊዜ ምርት የተቀናጀ የግብርና ስራ የሚሰጡ የማሽላና በቆሎ ሰብሎች ምርት እና ምርታማነትን ማሳደግ ተችሏል። በቀጣይም የተቀናጀ የግብርና ስራን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ምርታማነት የሚያሳድጉ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ።
የኢትዮጵያ የከተማና ገጠር አስደናቂ የልማት ስኬት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ተሞክሮ የሚሆን ተምሳሌታዊ ተግባር ነው
Aug 30, 2026 345
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ) ፦የኢትዮጵያ የከተማና ገጠር አስደናቂ የልማት ስኬት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ተሞክሮ የሚሆን ተምሳሌታዊ ተግባር መሆኑን የአህጉር አቀፍ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ገለጹ። በአፍሪካ ሕብረት ልማት ኤጀንሲ የግብርናና የገጠር ትራንስፎርሜሽን ዋና ፕሮግራም ባለሙያ ክሌመንት አድጆርሎሎ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በከተሞችና መሠረተ ልማት ግንባታ አስደናቂ ለውጥ አስመዝግባለች። አዲስ አበባን ለመጀመሪያ ጊዜ ያዩት እ.ኤ.አ. በ1999 እንደነበር በማስታወስ አሁን ከተማዋ በአስደናቂ የለውጥ ስኬት ውስጥ እየተጓዘች መሆኗን ገልጸዋል። የመዲናዋ የልማት ስኬትና የኢትዮጵያ አየር መንገድ በርካታ የበረራ መዳረሻዎች አዲስ አበባን የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማዕከል በማድረግ ለቱሪዝምና አገልግሎት ዘርፍ ወሳኝ የኢኮኖሚ አቅም መፍጠሩን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የከተማና ገጠር አስደናቂ የልማት ስኬት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ተሞክሮ የሚሆን ተምሳሌታዊ ተግባር መሆኑን አንስተዋል። በአጀንዳ 2063 የቀጣናዊ ስትራቴጂክ ትንተናና እውቀት ድጋፍ ሰጪ ሥርዓት ዲፓርትመንት ኃላፊ ፖል ጉቲጋ በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ የከተማ ልማት ኢንቨስትመንት አስደናቂ ውጤት አምጥቷል ብለዋል። የአፍሪካ ከተሞችን ሁለንተናዊ ለውጥ በውጤታማ አፈፃጸም መምራት ከተቻለ የአህጉሪቷን ዕድገትና ብልፅግና በማሳለጥ የኢኮኖሚ መነቃቃትና አቅም በመፍጠር የዜጎችን ተጠቃሚነት እንደሚያረጋግጥ ገልጸዋል። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ ከተሞቿን በማስዋብ የፈጠረችው ጠንካራ የከተሜነት ምቹ የኢንቨስትመንት አቅም ለአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ጭምር በልምድና ተሞክሮነት የሚወሰድ አስደናቂ ውጤት መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ለከተማና ገጠር ውጤታማ ሽግግር በቀላል ዋጋ የማይተመን አካታች የልማት አቅጣጫ እንደሚሆን አንስተዋል። በዑጋንዳ ግብርና፣ የእንስሳት ኢንዱስትሪና ዓሳ ሀብት ሚኒስቴር የምግብና የሥነ ምግብ ዋስትና ረዳት ኮሚሽነር አሌክስ ባምቦና በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ ተሞክሮ ለሁላችንም የሚተርፍ ነው ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር፣ አዲሱ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያና ሌሎች ግዙፍ ፕሮጀክቶች ግንባታም ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም እየገነባች ለመሆኗ ማሳያ ነው ብለዋል።
በጅማ ከተማ የተደራጁት የቅዳሜ ገበያዎች የምርት ዋጋን በማረጋጋት ሸማቹን ተጠቃሚ እያደረጉ ነው
Aug 30, 2026 201
ጅማ ፤ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ከተማ በሰፊው ተደራጅተው ሥራ የጀመሩት የቅዳሜ ገበያዎች የሸቀጦችንና የምግብ እቃዎችን ዋጋ በማረጋጋት ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያበረከቱ መሆኑን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። አላስፈላጊ የዋጋ ንረት ለመግታት እና አነስተኛና መካከለኛ ገቢ ያለውን የህብረተሰብ ክፍል ለመደገፍ መንግሥት በቀጥታ ከአምራቾች፣ ከገበሬዎች እና ከህብረት ሥራ ማህበራት ምርቶችን የሚያቀርቡ የቅዳሜ እና የእሁድ ገበያዎችን በተለያዩ ከተሞች እንዲስፋፉ የማድረግ አቅጣጫ አስቀምጦ ሲሰራ ቆይቷል። የጅማ ከተማ አስተዳደርም የኑሮ ውድነቱን ለማቃለል እና የገበያ ስርዓቱን ለማረጋጋት የቅዳሜ ገበያዎችን በከተማዋ የተለያዩ ክፍሎች በሰፊው በማደራጀት ወደ ሥራ አስገብቷል። እነዚህ ገበያዎች አምራቾችና የህብረት ሥራ ማህበራት ያለምንም ደላላ ጣልቃ ገብነት ምርቶቻቸውን በቀጥታ ለሸማቹ እንዲያቀርቡ ዕድል ፈጥረዋል። ይህም በከተማዋ የሚታየውን ሰው ሰራሽ የዋጋ ጭማሪ በመቀነስ፣ ሸማቾች ጥራት ያላቸውን ምርቶች በተመጣጣኝና በፍትሐዊ ዋጋ እንዲያገኙ በማድረግ ረገድ አዎንታዊ ውጤት እያስገኘ ይገኛል። በዚሁ ጉዳይ ላይ አስተያየታቸውን ለኢዜአ ያካፈሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ቀደም ሲል የቅዳሜ ገበያ በጥቂት ቦታዎች ብቻ ይካሄድ ስለነበር ከፍተኛ መጨናነቅና መገፋፋት ይፈጠር ነበር ብለዋል። አሁን ላይ የገበያ ቦታዎቹ በሰፊው መደራጀታቸው ይህንን እንግልት ማስቀረቱን አስረድተዋል። የጅማ ከተማ ነዋሪዋ አስማ መሀመድ የቅዳሜ ገበያው በየቀበሌያቸው በቅርበት በመደራጀቱ ያለምንም እንግልትና በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመት መቻሏን ገልጻለች። ልዩ የቅዳሜ ገበያው በከተማዋ የሚስተዋለውን የዋጋ ግሽበት በመግታትና ገበያውን በማረጋጋት ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተወጣ መሆኑን የገለጹት ደግሞ ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ከሚሳ ሀይሉ ናቸው። በዚሁ ገበያ ከመደበኛው የገበያ ዋጋ በቀነሰ ዋጋ መሸመት መቻላቸው ለህብረተሰቡ ትልቅ እፎይታ መፍጠሩንም አክለው ተናግረዋል። በገበያው ውስጥ በፀጥታ አካላትና በከተማው ንግድ ጽሕፈት ቤት ተወካዮች አማካኝነት ሰፊና ቀጣይነት ያለው ክትትል በመደረጉ ምክንያት ጥራታቸው የተጓደሉ ምርቶች ለህብረተሰቡ እንዳይቀርቡ ማስቻሉንም አቶ ከሚሳ ገልጸዋል። ሌሎች የከተማዋ ነዋሪዎች የሆኑት ወይዘሮ ደሜ ሀይሉ እና አቶ ሙሌ ተመስገን በበኩላቸው ልዩ የቅዳሜ ገበያ የዕለት ተዕለት ኑሯቸውን ቀላል እና የተረጋጋ እንዳደረገላቸው ይገልጻሉ። ወጣት ስንታየሁ ምሳው እንዳለው የቅዳሜ ገበያው ለሸማቾች ከሚሰጠው እፎይታ ባሻገር ለአምራች ወጣቶችም ሰፊ የገበያ ትስስር ፈጥሯል። የጅማ ከተማ ንግድ ጽህፈት ቤት ሀላፊ ወይዘሮ ረውዳ ጀማል በከተማዋ ከዚህ ቀደም በዘጠኝ ቦታዎች ብቻ ተወስኖ የነበረውን ልዩ የቅዳሜ ገበያ በ10 ቀበሌዎች በማስፋት ቁጥሩን ወደ 29 ማድረስ መቻሉንተናግረዋል። የገበያ ቦታዎቹ እንዲስፋፉ መደረጉ የህብረተሰቡን እንግልት ለመቀነስ እና ፍትሐዊ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ ታስቦ መሆኑንም ኃላፊዋ አስረድተዋል። አክለውም ከከተማዋ ውጭ ከሚገቡ ምርቶች ጎን ለጎን ከአካባቢው አምራቾች ጋር ሰፊ የገበያ ትስስር መፈጠሩንና እንዲያመርቱም ተገቢው ማበረታቻ መደረጉን ገልጸዋል። የቅዳሜ ገበያዎችን ቁጥር በማሳደግ ምርቶችን በቅርበትና በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ የማቅረብ ሥራ በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ወይዘሮ ረውዳ ገልጸዋል።
በመደመር መንግሥት ዕይታ አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት የማድረግ ራዕይ ተጨባጭ ውጤት አምጥቷል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Aug 30, 2026 183
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ) ፦በቀጣይ አምስት ዓመታት በዘላቂ የልማት ሥራዎች ላይ አፈፃፀማችንን በማላቅ ሕዝባችን የሰጠንን ሀላፊነት በብቃት መወጣት ይኖርብናል ሲሉ የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቀጣይ አምስት ዓመትና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ በየደረጃው ባሉ የከተማ አስተዳደሩ የሥራ ኃላፊዎች ውይይት እየተደረገበት ነው። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ ሕዝባችን ያለፈውን ስትራቴጂያዊ ዕቅድ በሚገባ በመፈጸማችን ለቀጣዩ አምስት ዓመታት በድጋሚ እንድናገለግል ድምፁን ሰጥቶናል። በመሆኑም በቀጣዩ አምስት ዓመታት በዘላቂ የልማት ሥራዎች ላይ አፈጻጸማችንን በማሳደግ፣ ሕዝባችን የሰጠንን ኃላፊነት በብቃት መወጣት ይኖርብናል ብለዋል። ከ2019 እስከ 2023 በሚተገበረው የአምስት ዓመቱ ስትራቴጂክ ዕቅድ ላይ ሁሉም አመራር የጠራ ግንዛቤ ኖሮት፣ የከተማዋን የብልጽግና ራዕይ የማሳካት የሕዝብ ኃላፊነት እንዳለበት ገልጸዋል። ሕዝቡ አምኖ እንደገና እንደመረጣቸው የገለጹት ከንቲባ አዳነች፣ የሥራ ባህላችንን በማሳደግ ለዜጎች የገባነውን ቃል የምንፈጽምበት ነው ብለዋል። ቀጣይነትን መሠረት ያደረገ የሥራ ባህልን ማሳደግና ያለፉ ድክመቶችን በማረም፣ ጥንካሬዎችን በማስቀጠል የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥን ማሳለጥ እንደሚገባ ገልጸዋል። በዕቅዳችን ላይ ተግባቦት መፍጠርና የተግባባንበትን በብቃት መፈጸም ይጠበቅብናል ብለዋል። በመደመር መንግሥት ዕይታ አዲስ አበባን የብልጽግና ተምሳሌት የማድረግ ራዕይን በተባበረ ክንድ የማሳካት ተግባር ተጨባጭ ውጤት ማምጣት እንዳስቻለ ገልጸዋል።
በጋምቤላ ክልል ለአሳ አጥማጆች የተደረገው የግብአት ድጋፍ አበረታች ውጤት እያስገኘ ነው
Aug 30, 2026 102
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 24/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል ለአሳ አጥማጆች የተደረገው የግብአት ድጋፍ አበረታች ውጤት እያስገኘ መሆኑን የክልሉ እንስሳትና ዓሳ ሃብት ልማት ቢሮ ገለጸ፡፡ በጋምቤላ ክልል የሚገኙት ታላላቅ ወንዞችና የውሃ አካላት ክልሉን በዓሳ ሀብት ከፍተኛ አቅም ካላቸው የኢትዮጵያ አካባቢዎች አንዱ ያደርጉታል። ክልሉ በዓመት በሺዎች ቶን የሚቆጠር ዓሳ የማምረት አቅም ቢኖረውም፣ ዘርፉ ለብዙ ዓመታት በባህላዊ የአሳ ማጥመድ ዘዴዎችና በግብአት እጥረት ምክንያት የሚገባውን ያህል ጥቅም ሳይሰጥ ቆይቷል። በክልሉ የሚገኙ አሳ አጥማጆች ዘመናዊ የዓሳ ማጥመጃ መረቦች፣ የጀልባዎችና የበረዶ ሳጥን አቅርቦት እጥረት ስለነበረባቸው፣ እንዲሁም ከምርት በኋላ የሚባክነውን የዓሳ መጠን የመቀነስና የገበያ ትስስር የመፍጠር ክፍተቶች ነበሩባቸው። ይህን ክፍተት ለመሙላት የጋምቤላ ክልል እንስሳትና ዓሳ ሃብት ልማት ቢሮ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ትኩረት ሰጥቶ ሲሰራ ቆይቷል። ቢሮው ለአሳ አጥማጆችና ለተደራጁ ማህበራት የቁሳቁስና የግብአት ድጋፍ ከመስጠቱም በላይ፣ በዘመናዊ የዓሳ አመራረት፣ አያያዝ፣ ጥራት አጠባበቅና ጥበቃ ዙሪያ ተከታታይ የሙያና ቴክኒክ ስልጠናዎችን ሲሰጥ ቆይቷል። የክልሉ እንስሳትና ዓሳ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ክርምስ ሌሮ እንዳረጋገጡት፣ እነዚህ የተደረጉት የግብአት አቅርቦቶችና የሙያ ድጋፎች አሳ አጥማጆቹ አሰራራቸውን ከባህላዊ ወደ ዘመናዊ እንዲያሸጋግሩ፣ የምርት መጠናቸውን እንዲጨምሩ እና የቤተሰቦቻቸውን ገቢ በማሻሻል የአካባቢውን ኢኮኖሚ እንዲያነቃቁ አስችለዋል። በተለይም የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ተግባራዊ መደረጉ ዘርፉን በእውቀት በመምራት የአስጋሪዎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ማገዙን ገልጸዋል። በክልሉ የአሳ ልማትን ውጤታማ ለማድረግ በወንዞች፡ በሃይቆችና ሰው ሰራሽ የውሃ አማራጮች ጭምር በመተግበር የዘርፉን ኢኮኖሚያዊ አቅም ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 5 ሺህ 970 ቶን አሳ ምርት ታቅዶ ከእቅድ በላይ 10 ሺህ 840 ቶን ማምረት መቻሉን ገልጸዋል። የዓሳ ሃብት ልማቱን ለስራ እድል ፈጠራ ለማዋል በተደረገው ጥረትም በማህበር ለተደራጁ ወጣቶች የዓሳ ማስገሪያ፡ ማቀናባሪያና የማጓጓዣ ግብዓቶች እንዲያገኙ መደረጉንም ተናግረዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ዘርፉን ይበልጥ ለማሳደግ ከሌማት ቱትሩፋት መርሃግብር ጋር አቀናጅቶ እንደሚሰራም ገልጸዋል። በአኝዋሃ ዞን በአቦቦ ወረዳ የሪዮ ቤር ዓሳ አምራች ማህበር አባል ወጣት ዳክ ኡጉት፤ የዓሳ ማስገሪያና የትራንስፖርት ድጋፍ በማግኘታቸው የዓሳ ምርታቸውን በጥራትና በወቅቱ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ተናግሯል። የዓሳ ምርታማነታቸውን በጥራትና በብዛት ለገበያ በማቅረብ ተወዳዳሪነታቸውን ማሳደግ እንደቻሉ የገለጸው ደግሞ ሌላው የማህበሩ አባል ወጣት ጆክ ኡፑቲ ነው።
በሶማሌ ክልል የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች በተቀናጀ መልኩ እየተከናወኑ ነው - ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ
Aug 29, 2026 199
ጅግጅጋ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል የተቋማትና የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች በተቀናጀ መልኩ እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ፤ የክልሉን ኢንቨስትመንትና የኢንዱስትሪና ቢሮ አዲስና ዘመናዊ የህንፃ ግንባታ አስጀምረዋል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ባደረጉት ንግግርም በክልሉ የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሁለንተናዊ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። ከልማት ስራዎች በተጓዳኝ የመንግስት አገልግሎቶችን ምቹ፣ ፈጣንና ቀልጣፋ የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን አንስተዋል። በዛሬው እለትም የክልሉን ኢንቨስትመንትና የኢንዱስትሪና ቢሮ አዲስና ዘመናዊ የህንፃ ግንባታ መጀመሩን ገልጸው፤ የተቋማትና የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች ይቀጥላሉ ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን የትምህርት፣ የውሃ፣ የመንገድ፣ የጤና የዲጂታል ልማትና ሌሎችም ስራዎች በልዩ ትኩረት እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። በክልሉ ከተሞችም ይሁን በገጠር ሰው ተኮር የሆኑ ልማቶችን የመገንባትና የዜጎችን ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራ ዋነኛ ትኩረታችን ሆኖ ይቀጥላል ብለዋል።