ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በጋምቤላ ክልል ከ7 ሺህ 98 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ ሆኗል
Jul 23, 2026 48
ጋምቤላ፤ ሀምሌ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ7 ሺህ 98 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ መደረጉን የክልሉ ማዕድን ቢሮ አስታወቀ። የጋምቤላ ክልል ማዕድን ቢሮ ኃላፊ አቶ ቻም ኡበንግ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዘርፉ በተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ ውጤቶች ተመዝግበዋል። በበጀት ዓመቱ 6 ሺህ ኪሎ ግራም ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ ለማድረግ ታቅዶ ከ7 ሺህ 98 ኪሎ ግራም በላይ ወርቅ ገቢ መደረጉን ተናግረዋል። በክልሉ በበጀት ዓመቱ ገቢ የተደረው የወርቅ ምርት ከእቅዱ በ1 ሺህ 98 ኪሎ ግራም ብልጫ ያለው ሲሆን ከቀዳሚው ዓመት ጋር ሲነፃፀር ደግሞ በ1 ሺህ 669 ኪሎ ግራም ብላጫ ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ለተመዘገበው ውጤት መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት የቁጥጥር፣ የክትትልና የድጋፍ ስራዎች ተጠናክረው በመከናወናቸው መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ በበጀት ዓመቱ በተከናወነው የማዕድን ሃብት ልማት ከ6 ሺህ 890 በላይ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል የተፈጠረላቸው መሆኑንም የቢሮ ሃላፊው ገልጸዋል።
በሲዳማ ክልል አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ያደረጉ የፍራፍሬ ልማት ስራዎች እየተካሔዱ ነው
Jul 23, 2026 50
ሃዋሳ፤ ሃምሌ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ያደረጉ የፍራፍሬ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ቡና ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ልማት ባለስልጣን አስታወቀ፡፡ የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ መስፍን ቃሬ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤በክልሉ የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጥና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ፍራፍሬዎችን በማልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ተችሏል። በክልሉ ካለው የፍራፍሬ ማሳ 43 ከመቶው በአቮካዶ ተክል የተሸፈነ ሲሆን የአፕልና አናናስ ተክልም የቤተሰብ ብልጽግና ፓኬጅ አካል ሆኖ እየተሰራበት ይገኛል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅትም በአቮካዶ ልማት የተሳተፉ ከ40 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ምርታቸውን ለይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ ዘይት አምራች ፋብሪካዎች እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለዚህም በየዓመቱ የተሻሻሉ ችግኞች በመትከል ምርታማነትን የማሳደግ ስራ እየተከናወነ ሲሆን በተያዘው ዓመትም የ4 ነጥብ 5 ሚሊዮን ችግኞች ተከላ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡ በክልሉ የጣራሜሳ አካባቢ አትክልትና ፍራፍሬ አምራችና አቅራቢ መሰረታዊ ህብረት ስራ ማህበር ሰብሳቢ አቶ ኩዬሬ ሁሬሳ፤ በአቮካዶ ልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችንን እያረጋገጥን ነው ብለዋል፡፡ በ2011 ዓ.ም 320 አርሶ አደሮችን በማቀፍ የተመሰረተው ማህበሩ፤በዋናነት ከአቮካዶ ምርት በተጨማሪ ቲማቲም፣ ጥቅል ጎመንና ሌሎች አትክልቶችን ከማምረት ባሻገር ችግኞችንም እንደሚያፈሉ ነው የተናገሩት። ማህበራቸውን ወክለው ጣሊያን ሃገር በተካሄደ አውደ ርዕይ በመሳተፍም የገበያ ትስስር ለመፍጠር እንደቻሉም ነው የሚገልጹት። በአሁኑ ወቅም በዓመት ሁለት ጊዜ የሚሰበስቡትን የአቮካዶ ምርት ለይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንደስትሪ ፓርክ እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል። ዘንድሮም ከ200 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ የአቮካዶ ምርት ለማቅረብ ማቀዳቸውን የጠቆሙት አርሶ አደሩ፤ ለተከላ የሚሆኑ ከ10 ሺህ በላይ የተሻሻሉ የአቮካዶ ችግኞችን ለአካባቢው አርሶ አደሮች ማሰራጨታቸውን ተናግረዋል፡፡
የባሕርዳር ከተማን የተሞክሮ ማዕከል ለማድረግ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ እየተደረገ ነው
Jul 23, 2026 66
ባህርዳር፤ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፡-የባህር ዳር ከተማ የልማትና እድገት የተሞክሮ ማዕከል ለማድረግ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የአማራ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሞላ መልካሙ(ዶ/ር) ገለጹ። የባህርዳር ከተማ አስተዳደር የከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት አፈጻጸምን የሚገመግምና የአዲሱ በጀት ዓመት እቅድ ትውውቅ መድረክ ዛሬ አካሂዷል። የቢሮ ኃላፊው ሞላ መልካሙ(ዶ/ር) እንደገለጹት በክልሉ የሚገኙ በርካታ ከተሞችን ለንግድ፣ ቱሪዝምና ለኑሮ የተመቹ ለማድረግ ሁለገብ የልማት ስራ እየተከናወነ ይገኛል። የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን በማከናወን ውብ፣ ሳቢና ማራኪ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የባህር ዳር ከተማ በሰፋፊ የአስፋልት መንገዶች፣ በኮሪደር ልማት፣ በስማርት ሲቲ ትግበራ፣ የአረንጓዴ ልማትና ሌሎች የልማት ስራዎች ካሳየችው እድገት በመነሳት የተሞክሮ ማእከል ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። እየተካሄደ የሚገኘው ሁሉን አቀፍ ልማት ከተማዋን ለኢንዱስትሪ፣ ኮንፈረንስ ቱሪዝም፣ ንግድና ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ምቹ ሁኔታ የፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል። ቢሮው በከተማዋ የሚካሄዱ የልማት ስራዎች በጥራትና በፍጥነት እንዲከናወኑ እያደረገ ያለውን ክትትልና ድጋፍ አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ አቶ አስሜ ብርሌ በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በከተማዋ እየተገነቡ ያሉ የልማት ስራዎች ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ የሰጡ ናቸው ብለዋል። የተገኙ ስኬቶችን አጠናክሮ በማስቀጠል በቀጣይ የዲጂታል መሠረተ ልማትን የበለጠ በማስፋፋት የአገልግሎት አሰጣጥ ችግርን ለመቅረፍ በተሻለ መንገድ እንደሚሰራ አስገንዝበዋል። በበጀት ዓመቱ የተመዘገቡ ስኬቶች የሁሉም ባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ሥራ ውጤት ናቸው ያሉት ደግሞ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የከተማ አስተዳደሩ ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ስራ አስኪያጅ አቶ ተሻገር አዳሙ ናቸው። በመጀመሪያውና 2ኛው ዙር ብቻ ስምንት ነጥብ ስድስት ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ማጠናቀቅ መቻሉን ጠቁመው 3ኛው ዙርም በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ አረጋግጠዋል። የተቀናጀ የኮሪደር ልማት ሥራዎችን በማፋጠን የባሕርዳር ከተማን ሁለንተናዊ ተመራጭነት በተጨባጭ የማረጋገጥ ጉዳይ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል። በ2019 በጀት ዓመት የታቀዱ የልማት ሥራዎችን በጥራትና በፍጥነት በማከናወን የከተማዋን ህዝብ ተጠቃሚ ለማደረግ በቅንጅት እንደሚሰራ አስገንዝበዋል። በመድረኩ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች፣ ባለሙያዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላተ ተሳትፈዋል።
በአሪ ዞን የመኸር አዝመራን ስኬታማ ለማድረግ የግብአት አቅርቦትና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ላይ እየተሰራ ነው
Jul 23, 2026 177
ጂንካ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ በአሪ ዞን የመኸር አዝመራን ስኬታማ ለማድረግ የግብአት አቅርቦትና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ላይ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ ። በዞኑ የ2018/19 የመኸር አዝመራ የማስጀመሪያ መርሃ- ግብር እየተካሄደ ነው። የአሪ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ገረመው ኃይለማርያም በዚሁ ወቅት እንዳሉት የግብርና ዘርፉን በማዘመን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የስራ እድል ፈጠራን ለማስፋት እየተሰራ ነው ። በዞኑ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ የተሻለ የግብአት አቅርቦት እንዲኖር ከማድረግ ባለፈ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማጎልበት ሞዴል አርሶ አደሮችን ለማፍራት እየተቻለ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ በበጋው ወራት የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የመኸር አዝመራውን ውጤታማ ለማድረግ መደላድል ፈጥረዋል ነው ያሉት። የአሪ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ጉራልቅ ይዥማልቅ በበኩላቸው፤ በዞኑ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖን የሚቋቋም ግብርናን እውን በማድረግ ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃን ጨምሮ የአረንጓዴ ልማት ስራዎች በተለየ ትኩረት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ግብርናን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ በመስኖ ልማት ላይ ትኩረት ለማድረግም የገፀ ምድርና የከርሰ ምድር የውሃ አማራጮች ጥቅም ላይ መዋላቸውን አስረድተዋል። የመኸር አዝመራውን በታቀደው ልክ ስኬታማ ለማድረግም አርሶ አደሮች የግብርና ባለሙያዎችን ምክር በመቀበል፣ የተሻሻሉ ዝርያና ቴክኖሎጂዎችን እንዲጠቀሙ እየተደረገ ነው ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ ከጂንካ ዩኒቨርስቲ ፣ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ፣ከጂንካ ግብርና ምርምር ማዕከል እና የአጋር ድርጅት ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የኢትዮ-ቴሌኮም ቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የመሪነት ሚና መወጣት የሚያስችል ነው
Jul 23, 2026 154
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮ-ቴሌኮም ቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የመሪነት ሚና መወጣት የሚያስችል መሆኑን የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ገለጹ። የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ የተቋሙን የ2018 በጀት ዓመት እና የቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ አፈፃፀም አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ በሰጡት መግለጫ፣ ኢትዮ ቴሌኮም ባለፉት ሰባት ዓመታት ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በትጋት ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮም በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት 215 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ገቢ በማግኘት የእቅዱን 99 ነጥብ 7 በመቶ ማሳካቱንም ገልጸዋል። ይህ ገቢ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ33 ነጥብ 2 በመቶ እድገት ያሳየ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት የቴሌብር ተጠቃሚዎች ቁጥር 60 ነጥብ 5 ሚሊዮን መድረሱን አስታውቀዋል ። ባለፈው ዓመት የተጀመረውና ለሶስት ዓመታት የሚተገበረው የቀጣዩ አድማስ ስትራቴጂ ሁለንተናዊ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገትን ለማፋጠን ያለመ መሆኑን አስገንዝበዋል። ስትራቴጂው ተቋሙ በአፍሪካ የዲጂታል ኢኮኖሚ ውስጥ የድርሻውን እንዲወጣ የሚያስችልና ለአፍሪካ አጀንዳ 2063 ብሎም ለዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 መሳካት ጠንካራ መሰረት የሚጥል መሆኑንም ተናግረዋል። በስትራቴጂው የአንድ ዓመት አፈፃፀም በርካታ የኔትወርክ ተደራሽነት እና የማዘመን ስራዎች መከናወናቸውን አብራርተዋል። በዚህም 603 አዳዲስ የሞባይል ጣቢያዎች ተገንብተው ወደ ስራ መግባታቸውን ገልጸው፣ ይህም አጠቃላይ የሞባይል ጣቢያዎችን ቁጥር 10 ሺህ 613 ማድረሱን ተናግረዋል። በ195 የገጠር ሞባይል ጣቢያዎች መገንባታቸውንም በዚህም 117 ወረዳዎች ተደራሽ መሆናቸውን ገልፀዋል። ይህም ተደራሽነትን ማስፋትና አካታችነትን ማረጋገጥ ማስቻሉን ነው ዋና ስራ አስፈፃሚዋ የገለፁት። በ195 የገጠር ሞባይል ጣቢያዎች በመገንባታቸው 117 ወረዳዎች ላይ የኔትወርክ ተደራሽነትን በማስፋት አካታችነትን ማረጋገጥ ያስቻለ ትልቅ ስኬት መሆኑን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ 264 ከተሞች የአራተኛው ትውልድ (4ጂ) ኔትወርክ አገልግሎት ማግኘት መቻላቸውን ተናግረዋል። ሰባት ተጨማሪ ከተሞች የ5ጂ አገልግሎት ማግኘታቸውን ተከትሎም፣ የ5ጂ ተጠቃሚ ከተሞች ቁጥርም 33 መድረሱን አስታውቀዋል። በአጠቃላይ ሁለንተናዊ የቴክኖሎጂ እና የመሠረተ ልማት ማስፋፊያ ስራዎችን መሠረት በማድረግ፣ የኢትዮ ቴሌኮም አጠቃላይ የደንበኞች ቁጥር 90 ነጥብ 1 ሚሊዮን መድረሱን ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ ገልጸዋል።
በጅማ ዞን ከ1 ሺህ 600 በላይ አርሶ አደሮች ወደ ኢንቨስትመንት ተሸጋግረዋል
Jul 23, 2026 96
ጅማ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ በ2018 በጀት ዓመት በጅማ ዞን ከ1 ሺህ 600 በላይ አርሶ አደሮች ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን የዞኑ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ወይዘሮ ዘሊካ ቡላ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በዞኑ ለኢንቨስትመንት ያለውን አቅም ወደ ልማት ለመቀየር የአሠራርና የሕግ ማዕቀፎች ተዘርግተዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ በግብርና፣ አነስተኛና ጥቃቅን ኢንተርፕራይዞችና በኅብረት ሥራ ማኅበራት ተሰማርተው የነበሩ 1 ሺህ 739 አልሚዎች ሀብት አፍርተው ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ገልጸዋል። ባለሀብቶቹ ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩት 5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ካፒታል በማስመዝገብ መሆኑን ጠቁመዋል። አልሚዎቹ በተሰማሩበት ዘርፍ ውጤታማ ሆነው ወደ ኢንቨስትመንት እንዲሸጋገሩ በመንግሥት 8 ሺህ 27 ሄክታር መሬት የቀረበ ሲሆን፣ 120 ሚሊዮን ብር ብድር መሰጠቱን ገልጸዋል። ፕሮጀክቶቹ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገቡም ከ22 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች በቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ይፈጥራሉ ብለዋል። በዞኑ 2 ሺህ 495 የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች በሥራ ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው እነዚህ የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ከ55 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች በቋሚነትና በጊዜያዊነት የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ተናግረዋል። በዞኑ በዴዶ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ጃፈር አብዱልቃድር፤ በ2012 ዓ.ም ተደራጅተው በ50 ሺህ ብር መነሻ ካፒታል በግብርና ሥራ ላይ ተሰማርተው እየሠሩ እንደነበር ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ካፒታላቸውን በማሳደግና ትርፋማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ገልጸዋል። ማኅበራቸው ከ60 በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ጠቅሰው፣ በቀጣይም ሥራውን በማስፋት በርካታ ወጣቶችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ አቅደው እየሠሩ እንደሚገኙ አንሥተዋል። ወጣት ሚሊዮን ዳመነ በበኩሉ፤ በመንግሥት በተመቻቸላቸው የብድር አገልግሎት በሕንፃ ግንባታ ዘርፍ በማኅበር ተደራጅተው በመሥራት ካፒታላቸውን በማሳደግ ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገር መቻላቸውን ተናግሯል። በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ዞኑ ምቹ እና በርካታ አማራጮች ያለው ከመሆኑም ባሻገር መንግሥት የሚያደርግላቸው ድጋፍ እና ክትትል የበለጠ ለመሥራት ተነሣሽነትን እንደፈጠረላቸው አስታውቋል። በዞኑ በቀጣይ የኢንቨስትመንት ቅበላ አቅምን ለማሳደግ እየተሠራ መሆኑም ተጠቅሷል።
የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ዕድገት በማፋጠን ረገድ አበረታች ውጤቶችን አስመዝግቧል
Jul 23, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር በ75 ዓመታት ጉዞው የሀገሪቱን የልማት ምሰሶ በመደገፍ፣ የኢኮኖሚ ዕድገትን በማፋጠንና ማኅበራዊ ትስስርን በማጠናከር ረገድ አበረታች ውጤቶችን ማስመዝገቡን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥና የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የቦርድ ሰብሳቢ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የተመሰረተበትን 75ኛ ዓመት የአልማዝ ኢዮቤልዩ በዓሉን በተለያዩ መርሃ ግብሮች ማክበር ጀምሯል። በበዓሉ ላይ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥና የተቋሙ ቦርድ ሰብሳቢ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የቀድሞ የተቋሙ አመራሮችና ሠራተኞች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ገዥ እና የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር ኢዮብ ተካልኝ በዚሁ ወቅት፣ ሕብረተሰቡ በበጋም ሆነ በክረምት አገልግሎት የሚሰጥ መንገድ ለማግኘት ይጓዝ የነበረው አማካይ ርቀት ከ21 ኪሎ ሜትር ወደ 4 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር ዝቅ ማለቱን ገልጸዋል። ይህ አፈጻጸም የመንገድ ተደራሽነት ምጣኔውን በአምስት እጥፍ ያሻሻለ ትልቅ ስኬት መሆኑን ጠቁመዋል። በቅርብ ዓመታት ውስጥ 44 ሺህ በላይ ኪሎ ሜትር መንገድ መገንባቱን ጠቅሰው ይህም የሀገሪቱን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እና የሕዝቦችን ማኅበራዊ መስተጋብር በከፍተኛ ደረጃ ማጠናከሩን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም የሀገር ውስጥ ኮንትራክተሮችን አቅም ማሳደግ፣ በቴክኖሎጂ የተደገፉ አሠራሮችን ማስፋፋት እና የአካባቢ ጥበቃን ያገናዘበ ግንባታዎችን ከማካሄድ አኳያም ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ ተቋሙ ላለፉት 75 ዓመታት የሀገሪቱን የልማት ምሰሶ በመደገፍ፣ የኢኮኖሚ እድገትን በማፋጠንና ማኅበራዊ ትስስርን በማጠናከር ረገድ አበረታች ስራዎችን ሰርቷል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር በ75 ዓመታት ጉዞው ጠንካራ ተቋማዊ መዋቅር፣ አሠራር እና ትውልድ ተሻጋሪ እውቀት የገነባ አንጋፋ ተቋም መሆኑንም ጠቅሰዋል። የአስተዳደሩ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መሐመድ አብዱራህማን፣ የመንገድ መሠረተ ልማት ግንባታ ሕዝቦችን የሚያቀራርብ፣ ገበያን የሚያስፋፋና የሀገር አንድነት መሠረትን የሚያጠናክር መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ የመንገድ አውታሩ መስፋፋት የገበሬውን ምርት ወደ ገበያ፣ ተማሪዎችን ወደ ትምህርት ቤት፣ ህሙማንን ደግሞ ወደ ሕክምና ተቋማት በቀላሉ ለማድረስና የኢንቨስትመንት ፍሰቱን ለማፋጠን መሠረታዊ ኃይል ሆኗል ሲሉም አክለዋል። ተቋሙ ከግንባታ ሥራዎች ጎን ለጎን የሀገር ውስጥ የመሐንዲስነት አቅምን በማጠናከር፣ የፕሮጀክት አስተዳደር ሥርዓቶችን በማዘመንና ዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን አሠራር ውስጥ በማስገባት ተቋማዊ ብቃቱን ከፍ ማድረጉን ተናግረዋል። ለተቋሙ ስኬት መሠረት ለጣሉ የቀድሞ አመራሮችና በአስቸጋሪ መልክዓ ምድራዊ ሁኔታዎችና አየር ንብረት ውስጥ በመስክ ላይ ተሰማርተው መሠረተ ልማቱን ለገነቡ መሐንዲሶች፣ ቴክኒሻኖችና የመስክ ሠራተኞች ምስጋና አቅርበዋል።
በምሥራቅ ሸዋ ዞን የቡና ልማትን ለማላመድና ለማስፋፋት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jul 23, 2026 84
አዳማ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ሸዋ ዞን የቡና ልማትን ለማላመድና ለማስፋፋት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፣ በክልሉ ከሚገኙ ዞኖች መካከል ምሥራቅ ሸዋ ዞን ቀደም ሲል በቡና ልማት የማይታወቅ ነበር። ይህንን ሁኔታ ለመቀየርም የዞኑ አስተዳደርና ግብርና ጽሕፈት ቤት በቁርጠኝነት እየሠሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በዚህ ረገድ የመጣ የተሻሻለ የቡና ዝርያ በዞኑ በሚገኙ ሁለት የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እየተዘጋጀ መሆኑን ጠቅሰው፣ እስካሁንም 800 ሺህ የቡና ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን አብራርተዋል። የቡና ልማቱን በአጠቃላይ በግብርና ኢኒሼቲቭ መሠረት ለማስፋፋት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑንም አቶ አብነት አመላክተዋል። አዳማ፣ ሉሜ፣ ቦራ፣ አዳሚ ቱሉ፣ ዱግዳ እና መተሐራ አካባቢ በተመረጡ ቦታዎች የቡና ልማቱን ለማላመድና ለማስፋፋት ሰፊ ርብርብ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በልማቱ የሚሳተፉ አርሶ አደሮች ልየታ ተደርጎ፣ የቡና ችግኝ መትከያ ጉድጓዶች በሳይንሳዊ ዘዴ በየደረጃው እየተዘጋጁ እንደሆነ ገልጸዋል። በዚህም ለመጀመሪያ ጊዜ በዞኑ 200 ሄክታር አዲስ መሬት በቡና እንደሚሸፈን አመልክተዋል። ከዚህ ቀደም የቡና ተክል በተበታተነ መልኩ ይተከል ከነበረበት አሠራር በመውጣት፣ በአዲስ ኢኒሼቲቭ በአንድ መንደር (በኩታገጠም) ለማልማት ታቅዶ በልዩ ትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። አካባቢው ለቡና ልማት ምቹ ሥነ-ምህዳር እንዳለው የጠቀሱት አቶ አብነት፣ አርሶ አደሮች ይህንን በመገንዘብ የቡና ልማትን ከሌሎች ሰብሎች ጎን ለጎን እንዲያካሂዱ ጥሪ አቅርበዋል። ጽሕፈት ቤቱም የተሻሻሉ የቡና ችግኝ ዝርያዎችን ከማቅረብ ጀምሮ አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።
በዞኑ 487 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር ተሸፍኖ እየለማ ነው
Jul 23, 2026 84
ገንዳውኃ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን በመኸር ወቅቱ እስካሁን 487 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር ተሸፍኖ እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ምክትል ኃላፊ አቶ ጤናው ፋንታሁን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ በ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት ለሰብል ልማቱ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በምርት ወቅቱ ከ529 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት ከ12 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። እስካሁን በተደረገ ጥረት 487 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር ተሸፍኖ እየለማ መሆኑን ጠቁመው ከዚህ ውስጥ ከ370 ሺህ ሄክታር በላዩ በትራክተር ታርሶ የተዘራ መሆኑን ተናግረዋል። እንዲሁም ከ250 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም የለማ መሆኑን አመልክተዋል። ከተዘሩ ሰብሎች ውስጥም ገበያ ተኮር የሆኑ ሰሊጥ፣ አኩሪ አተር፣ ጥጥ፣ ቦሎቄና ሌሎች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል። በምርት ወቅቱ ለወጭ ንግድ፣ ለኢንዱስትሪ ግብአትና ለአካባቢ ገበያ የሚሆኑ ሰብሎችም በስፋት እንደሚለሙ ተናግረዋል። በዞኑ በእርሻ ኢንቨስትመንት የተሰማሩት አሊ መሐመድ ፤ 60 ሄክታር መሬታቸውን በሰሊጥ፣ አኩሪ አተርና ሌሎች ሰብሎች በዘር መሸፈናቸውን ገልጸዋል። መሬታቸውን በትራክተር ደጋግመው በማረስ በመዝራታቸው ድካምና ወጪ የቀነሰላቸው መሆኑን ተናግረዋል። አርሶ አደር ደጀኔ ታደሰ በበኩላቸው፤ ኩታገጠም ማሳቸውን በሰሊጥ፣ አኩሪ አተርና ማሽላ ዘር መሸፈናቸውን ገልጸዋል። በዞኑ በ2017/18 ምርት ዘመን መኸር ወቅት ከ510 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት 10 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል ምርት መሰብሰቡን ከመምሪያው የተገኘ መረጃ ያሳያል።
በሁሉም ዘርፎች የሕዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማረጋገጥ የተጀመሩ ውጤታማ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jul 22, 2026 252
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦በሁሉም ዘርፎች የሕዝቡን ባለቤትነት እና ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ይበልጥ በማረጋገጥ የተጀመሩ ውጤታማ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ሲሉ የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት እና የዋና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አደም ፋራህ ገለጹ፡፡ የብልፅግና ፓርት የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ የውይይት መድረክ በአዲስ አበባ አካሂዷል። የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት እና የዋና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አደም ፋራህ በውይይቱ ላይ እንደገለጹት፤ በሁሉም ክልሎች በሁሉም ዘርፎች የተሻሉ አፈፃፀሞችና ዕድገቶች ተመዝግበዋል፡፡ ከሀገሪቷ ከፍተኛ አቅም እና ከህዝቡ ፍላጎት አኳያ አሁንም ብዙ መሰራት እንደሚጠበቅ በአጽንኦት ገልጸዋል። ህዝቡ በምርጫ ወቅት የሰጠውን ትልቅ እውቅና ያነሱት ምክትል ፕሬዝዳንቱ አቶ አደም፤ አሁን ላይ እንደ አገልግሎት አሰጣጥ፣ የስራ እድል ፈጠራ እና የኑሮ ውድነት ያሉትን አንገብጋቢ ጉዳዮች በቁርጠኝነት መመለስ እንደሚገባ ጠቅሰዋል፡፡ የስራ ዕድል ፈጠራ፣ የገበያ መረጋጋትና የኑሮ ውድነት ቅነሳ ከፍተኛ ትኩረት የተሰጣቸው ጉዳዮች በመሆኑ በሁሉም የአመራር በንቅናቄ መመራታቸውን ተናግረዋል፡፡ ይህም ከዕቅድ አፈጻጸም በሕዝቡ የዕለት ተዕለት ኑሮ ላይ ተጨባጭ ውጤቶች እንዲመዘገቡ ማስቻሉን አመልክተዋል። ፓርቲው ስራዎችን በህዝብ ንቅናቄ በመምራት ሰባት ዋና ዋና ፋይዳዎች ለማግኘት አስቦ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም ችግሮችን በየደረጃው ግብረ-ኃይል በማቋቋም እና መሪዎችን ግንባር ቀደም በማድረግ እስከ ታችኛው መዋቅር ድረስ በባለቤትነት መምራት ይገባል ብለዋል። በሁሉም ዘርፍ የህዝቡን ባለቤትነት እና የተደራጀ ተሳትፎ ማረጋገጥ እንደሚገባም ጠቁመው፤ በተጨማሪም የአስተሳሰብ ፣ የአደረጃጀት፣ የፋይናንስ፣ የግብዓት ማነቆዎችን እና ህገ ወጥ ደላሎችን በመለየት ተጠያቂነትን ማረጋገጥም ይገባል ብለዋል። በመጨረሻም የንቅናቄ ስራዎችን በሂደት ቋሚና ተቋማዊ በሆነ አሰራር መተካት እንደሚገባም ነው የገለጹት። የኑሮ ውድነትን ለማቃለል እና ገበያን ለማረጋጋት በማክሮ ኢኮኖሚ ከሚከናወኑ ስራዎች ጎን ለጎን እያንዳንዱ ቀበሌና ወረዳ የራሱን ተጨባጭ ሁኔታ በመጠቀም የምርት አቅርቦትን ማሳደግ፣ የህገወጥ ደላሎችን መረብ መበጣጠስ እና ንግድን በስርዓት መምራት ይኖርበታል ብለዋል፡፡ በተጨማሪም ከውጭ ሀገር ስራ ስምሪት ጋር ተያይዞ የሚሰጡ ስልጠናዎች እና የምዘና ሂደቶች (COC) ከዓለም አቀፍ ገበያ ፍላጎት ጋር እንዲጣጣሙ ማድረግ ይገባልም ብለዋል፡፡
ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራዎችን በማጠናከር የዜጎችን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል
Jul 22, 2026 258
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራዎችን በማጠናከር የዜጎችን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ አኳያ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባል ሙፈሪያት ካሚል ገለፁ። የብልፅግና ፓርቲ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማ እና የ2019 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ የውይይት መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባልና የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል በመድረክ ላይ እንደገለጹት፤ ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራዎችን በማጠናከር የዜጎች ተጠቃሚነትን ከማረጋገጥ አኳያ ውጤታማ ስራዎች ተከናውነዋል። በበጀት ዓመቱ የሀገር ውስጥ የሥራ ዕድል፣ የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት እና የቴክኖሎጂ አማራጮችን በመጠቀም የርቀት ሥራ በትኩረት መሰራቱን አንስተዋል። በዚህም መሠረት በሶስቱ ዋና ዋና አማራጮች ለአምስት ነጥብ አራት ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ ከአምስት ነጥብ ስድስት ሚሊዮን በላይ ማከናወን መቻሉን አብራርተዋል። ለዜጎች የተፈጠሩት የስራ እድሎች በግብርና፣ በአገልግሎት፣ በኢንዱስትሪ፣ በውጭ አገር የስራ ስምሪት እና በርቀት የተፈጠሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ይህ የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ የፓርቲው ቅርብ አቅጣጫና ድጋፍ እንዲሁም የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ጠቁመዋል፡፡ በውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት ከ 631 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ስምሪት በማመቻቸት ዜጎች ተጠቃሚ መሆናቸውን አመልክተዋል። ከተለያዩ የአረብ ሀገራት በተጨማሪ ወደ ስድስት የአውሮፓ ሀገራትም ዜጎችን መላክ መጀመሩን ጠቅሰዋል፡፡ ሀገራት እያሳዩ ባሉት ፍላጎት መሠረት ስምምነቶች ተፈራርመው ዜጎች አስፈላጊውን የሙያና የቋንቋ ስልጠና አግኝተው ወደ ሥራ እንዲሰማሩ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የዲጂታል እና የርቀት ሥራ (Remote Work) የዲጂታል ቴክኖሎጂን በመጠቀም በርቀት ሥራ ከ41ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉንም አብራርተዋል፡፡ ለዚህም የአምስት ሚሊዮን ኢትዮ-ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ጋር የተደረገ ማስተሳሰር ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ጠቅሰዋል፡፡ በተጨማሪም ወደ 70 የሚጠጉ የቴክኒክና ሙያ ማዕከላት የዲጂታላይዜሽን ፕሮግራም እንዲቀርፁ ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።
በ2018 በጀት ዓመት የምርት አቅርቦትን በዘላቂነት ለማሻሻል በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል
Jul 22, 2026 176
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦በ2018 በጀት ዓመት የምርት አቅርቦትን በዘላቂነት ለማሻሻል ከተከናወኑ ተግባራት እና የገበያ መሰረተ ልማትን በማስፋፋት ረገድ አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባል ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የብልፅግና ፓርቲ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማ እና የ2019 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ ላይ ሲካሄድ የቆየው የውይይት መድረክ ተጠናቋል። በዚህ መድረክ የፓርቲው ምክትል ፕሬዝዳንት እና የዋና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አደም ፋራህን ጨምሮ ሚኒስትሮች፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች እና የክልል አመራር አባላት ተሳትፈዋል። የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ አባልና የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ በበጀት ዓመቱ የኑሮ ውድነትን ለማቃለል እና ገበያን ለማረጋጋት በተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት እንዲሁም በቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ሪፖርት አቅርበዋል። በቀረበው ሪፖርት መሠረት የምርት አቅርቦትን በዘላቂነት ለማሻሻል ከተከናወኑ ተግባራት መካከል የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል ብለዋል። በበጀት ዓመቱ 15 ነጥብ 8 ቢሊዮን ሊትር የወተት ምርት መገኘቱን አመልክተው፤ ይህም ከእቅዱ እኳያ እጅግ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል። የነዳጅ አቅርቦትን በተመለከተ፤ ከዓለም አቀፍ የነዳጅ መስመር መዛባት እና የሆርሙዝ ሰርጥ መዘጋት ተግዳሮቶች ቢኖሩም ታቀዶ ከነበረው 5 ነጥብ 23 ሚሊዮን ሜትሪክ ኩብ የእቅዱን 91 በመቶ ነዳጅ ማቅረብ መቻሉን ተናግረዋል። በሕገ-ወጥ አሰራር እና በከፍተኛ የፍላጎት እድገት ምክንያት በገበያው ላይ ተግዳሮቶችን ለመፍታት ጥብቅ ቁጥጥር እየተደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የገበያ መሰረተ ልማትን በማስፋፋት ረገድ አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ በሀገር ደረጃ ከተለዩት 7 ሺህ 628 የአካባቢ ገበያዎች መካከል የ3 ሺህ 670ዎቹ የይዞታ ማረጋገጥ ሥራ ተጠናቋል ብለዋል። በተጨማሪም 804 አዳዲስ የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች እንዲሁም 32 ዘመናዊ የገበያ ማዕከላት ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። የግብይት ትስስርን ለማጠናከር 1 ሺህ 352 የሸማቾች ህብረት ሥራ ማህበራት በትስስሩ የተሳተፉ ሲሆን፤ ለነዚህ ማህበራት ከ3 ነጥብ 33 ቢሊዮን ብር በላይ የሚሆን የሪቮልቪንግ ፈንድ ድጋፍ መደረጉን አብራርተዋል። በተከናወኑ የበጎ አድራጎት ተግባራት ከ4 ነጥብ 3 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የማዕድ ማጋራት ተጠቃሚ የሆኑ ሲሆን፤ ከ20 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ እና የምግብ ድጋፍ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ከገበያ ጋር ተያይዞ ያሉትን ችግሮችን ለመፍታት በተደረገው ጥረት ሕገ-ወጥ ኬላዎችን የማንሳት ሥራ መከናወኑን ጠቁመው፤ ለኑሮ ውድነት መባባስ ምክንያት የሆኑ ችግሮች እየተቃለሉ መምጣታቸውን ገልጸዋል። በገበያ ቁጥጥር እና ሕግ ማስከበር ተግባራት፤ በሕገ-ወጥ ንግድ በተሰማሩ 347 ሺህ ነጋዴዎች ላይ እርምጃ መወሰዱንም ተናግረዋል። በነዳጅ በሕገ-ወጥ አሰራር በተሳተፉ 688 አካላት ፣የንግድና ፀጥታ አካላትን ጨምሮ ሕጋዊ እርምጃ የተወሰደ ሲሆን፤ 2 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሊትር በላይ ነዳጅ ተወርሶ 781 ሚሊዮን ብር በቅጣት ገቢ መደረጉን ገልጸዋል። በቀጣይ በ2019 በጀት ዓመት ምርትና አቅርቦትን ማጠናከርን ዋና ትኩረቱ ያደረገ ስትራቴጂካዊ አቅጣጫ መያዙን ገልጸው፤ በዚህም የሌማት ትሩፋትና የከተማ ግብርና እንቅስቃሴዎችን በልዩ ትኩረት የማስፋት ስራ እንደሚከናወን ጠቁመዋል። በሁሉም የምርት ዓይነቶች ላይ የ10 በመቶ እድገት ታሳቢ በማድረግ ለመስራት የተያዘ ሲሆን፤ ለሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት ልዩ ድጋፍ በማድረግና የገበያ ትስስርን በማጠናከር የግብይት ስርዓቱን ለማረጋጋት በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል። የገበያ መሰረተ ልማትን ማስፋፋት ሁለተኛው ዋና የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ጠቅሰው፤ እስከ 2019 ዓ.ም ድረስ ሙሉ ለሙሉ የይዞታ ማስከበርና ማረጋገጥ ስራዎችን የማጠናቀቅ እንዲሁም በህብረተሰብ ተሳትፎ ቢያንስ የ500 ገበያዎችን ደረጃ የማሻሻል ስራ ይሰራል ብለዋል። የእሁድና ቅዳሜ ገበያዎችን ቁጥር ወደ 3 ሺህ 439 ለማድረስ እቅድ መያዙን ጠቁመው፤ በግብይት ሰንሰለቱ ውስጥ ያሉ ፈታኝ ሁኔታዎችን በህግና አሰራር ብቻ ለመፍታት የቁጥጥርና የሬጉላቶሪ አቅምን የማሳደግ ስራ ትኩረት እንደሚሰጠው ተናግረዋል።
በዞኑ የመኸር አዝመራን ውጤታማ ለማድረግ ለኩታ ገጠም እርሻና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 22, 2026 267
ወልቂጤ ፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በጉራጌ ዞን የመኸር አዝመራን ውጤታማ ለማድረግ ለሰብል እንክብካቤ፣ ለኩታገጠም እርሻና ለግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ትኩረት መሰጠቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ ፡፡ በዞኑ በአበሽጌ ወረዳ የኩታ ገጠም የመኸር አዝመራ ልማት የመስክ ምልከታ ተደርጓል፡፡ የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ በወቅቱ እንደገለጹት፤ በዞኑ የመኸር ሰብልን ውጤታማ ለማድረግ በ177 ሺህ ሄክታር መሬት በኩታ ገጠም የተለያዩ ሰብሎች ለምተዋል፡፡ በኩታ ገጠም እርሻውም በቆሎ፣ ማሽላ፣ ገብስ፣ አተር፣ ባቄላ፣ ሩዝ እና ጤፍ በኩታ ገጠም እየለማ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ለግብአት አቅርቦት፣ ለባለሙያ ድጋፍ፣ ለሰብል እንክብካቤና ለግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ትኩረት ተሰጥቶ እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል ፡፡ የአበሽጌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ካሱ ጁሃር በበኩላቸው፤ በወረዳው በዘንድሮው የመኸር ወቅት ግብአትና የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴን በመጠቀም አርሶ አደሮች ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ የአበሽጌ ወረዳ የአቡኮ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ዘሪሁን ቱሉ፤ የግብርና ባለሙያዎች የሚያደርጉላቸውን ድጋፍ ተጠቅመው አራት ሄክታር ኩታ ገጠም መሬታቸውን በበቆሎ ማልማታቸውን ተናግረዋል። የበቆሎ ሰብሉን ከአረም እና ከበሽታ በመከላከል የተሻለ ምርት ለማግኘት እየሠሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አርሶአደር ሃይሉ ዴሲሳ በበኩላቸው፤ ሶስት ሄክታር የበቆሎ ማሳቸውን እየተንከባከቡ በመሆናቸው የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ አመላክተዋል። ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በ30 ሄክታር መሬት ጤፍን በኩታ ገጠም በማልማት እንክብካቤ እያደረጉ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ አርሶ አደር ዳዊት አሰፋ ናቸው። ምርታማነታቸውን ለማረጋገጥም የተሻሻለ የጤፍ ዝርያን መጠቀማቸውንና የባለሙያ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑን ተናግረዋል።
በዞኑ እየተካሔደ ያለው የኮሪደር ልማት ስራ ተጠናክሮ ቀጥሏል
Jul 22, 2026 100
ጎንደር፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በማእከላዊ ጎንደር ዞን የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የዞኑ ከተማ እና መሠረተ ልማት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው የ2018 ዓ.ም የእቅድ አፈፃፀም ግምገማና የ2019 ዓ.ም እቅድ ትውውቅ መድረክ በጎንደር ከተማ ዛሬ ተካሒዷል። የመምሪያ ኃላፊው አቶ ገድፍ ጌትነት በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ የለውጡ መንግስት አሻራ የሆነው የኮሪደር ልማት ከተሞችን በማዘመን ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እያደረገ ነው። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዞኑ ስር በሚገኙ በአራት የከተማ አስተዳደሮችና በዘጠኝ መሪ ማዘጋጃ ቤት ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ ማከናወን መቻሉን ገልጸዋል። ለኮሪደር ልማት ስራው ህብረተሰቡ ከ68 ሚሊዮን ብር በላይ አስተዋጽኦ በማድረግ ለልማት ያለውን ቁርጠኝነት ማረጋገጡን ገልጸዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ስራዎችን አጠናክሮ ከማስቀጠል ባለፈ፤በ2019 በጀት ዓመት የልማት ስራውን ወደ ሌሎች ከተሞች የማስፋፋት ስራ ትኩረት እንደሚሰጠው አንስተዋል። ከተሞችን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት ማዕከል ለማድረግ የተጀመረው የኮሪደር ልማት ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ያሉት ደግሞ በብልጽግና ፓርቲ የዞኑ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፋሲል ሠንደቁ ናቸው። ይህም ከተሞቹን በማዘመን ለነዋሪዎች፣ ለጎብኝዎችና ለንግድ የተመቹ ከማድረግ ባለፈ የክልሉን ገጽታ ለመገንባት ተደማሪ አቅም እንደሚሆኑ አስረድተዋል። በዞኑ የአንባ ጊዮርጊስ ከተማ አስተዳደር ከተማና መሠረተ ልማት ፅህፈት ቤት ዋና ስራ አስኪያጅ ዲያቆን ወልዴ ባዘዘው እንደገለጹት ፤ የኮሪደር ልማቱ የማሕበረሰቡን አኗኗር ለማዘመን የሚያስችል ነው። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በከተማ አስተዳደሩ በኮሪደር ልማት ሁለት ነጥብ አምስት ኪሎ ሜትር ደረጃውን የጠበቀ የሳይክልና የእግረኛ መንገድ መገንባት መቻሉን አመልክተዋል። ሌላው የጎንደር ዙሪያ ወረዳ የማክሰኝት መሪ ማዘጋጃ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ሙሉአለም ሙጨ በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማት ስራው ከተማዋን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ነው ብለዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም የኮሪደር ልማት ስራውን አጠናክሮ በማስቀጠል የከተማዋን እድገት ለማፋጠንና ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በመድረኩ ላይ በዞኑ የሚገኙ የከተማ አስተዳደሮች፣የወረዳ ከተማ አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በወረዳው የቅመማ ቅመም ልማትን ለማሻሻል እየተካሄደ ባለው የተቀናጀ ስራ ውጤት እየተገኘ ነው
Jul 22, 2026 176
ሚዛን አማን፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ሸካ ዞን የኪ ወረዳ የአርሶ አደሩን የቅመማ ቅመም ልማት ለማሻሻል ከግብርና ምርምር ማእከላት ጋር እየተካሄደ ባለው የተቀናጀ ስራ ውጤት እየተገኘ መሆኑ ተገለጸ። የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ ዳዊት ተሰማ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ወረዳው ለቅመማ ቅመም ያለውን ምቹ ሥነ-ምህዳርና ከፍተኛ የገበያ ተፈላጊነት በመጠቀም በዘርፉ የበለጠ ውጤት ለማስመዝገብ እየተሰራ ነው። በዚህም በወረዳው የአርሶ አደሩን ቅመማ ቅመም ልማት ለማሻሻል ከግብርና ምርምር ማእከላት ጋር እየተካሄደ ባለው የተቀናጀ ስራ ውጤት እየተገኘ መሆኑን ተናግረዋል። እስካሁን በተደረገ ጥረት ልማቱ ከ8ሺ200 ሄክታር በላይ መሬት ላይ መስፋፋቱን ተናግረዋል። አርሶ አደሩ የተሻሻሉ የቅመማ ቅመም ዝርያዎችን በኩታ ገጠም እንዲያለማ በመደረጉ ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉንም አመልክተዋል ። በዚህም በተለይ የቁንዶ በርበሬ እና እርድ አምራች አርሶ አደሮች የገቢ ምንጫቸው ማደጉን ጠቅሰዋል። በቀጣይም የልማት ሂደቱን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ዘመናዊ የምርት ማቀነባበሪያ ማሽኖች ለማቅረብ በቅንጅት እንደሚሰራ አመላክተዋል። አርሶ አደሮች በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ ቅመማ ቅመምን በማልማት ምርታቸውን ማሳደጋቸውን የገለጹት ደግሞ የወረዳው ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ መልካሙ ተስፋሁን ናቸው። በወረዳው የእርድና የቁንዶ በርበሬ ልማትን በማስፋፋት አርሶ አደሩ ከምርቱ ተጠቃሚ የሚሆንበት ስርአት ተግባራዊ መደረጉን ተናግረዋል። የወረዳው አርሶ አደሮች በበኩላቸው የኩታ ገጠም የቅመማ ቅመም የአስተራረስ ዘዴን በመጠቀም ምርታማነታቸውን ማሳደጋቸውን አንስተዋል። በወረዳው የኅብረት ፍሬ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር የሱፍ መሐመድና አርሶ አደር ይመር አበጋዝ በቁንዶ በርበሬ ልማት ተሰማርተው ከምርት ሽያጭ ገቢያቸውን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። አርሶ አደር አሊ ሞላ እና አወል እንድሪስ በበኩላቸው በእርድ ልማት ተሰማርተው ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። ምርቱ በገበያ ላይ ተፈላጊ በመሆኑ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። የእርድ ልማቱን በኩታገጠም መስራታቸው ለእንክብካቤና ለምርት አሰባሰብ ሂደቱ ምቹ መሆኑን የተናገሩት አርሶ አደሮቹ በቀጣይም የምርት ዝግጅት ሂደቱን በዘመናዊ ማሽን ለማካሄድ እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።
በዞኑ የተከናወኑ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ለንብ ማነብ ስራ ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል
Jul 22, 2026 111
፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሐረርጌ ዞን በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ እና እንክብካቤ ላይ በተከናወኑ ተግባራት የደንና የአፈር ለምነት በማሳደጉ ለንብ ማነብ ስራቸው ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው አርሶ አደሮች ገለጹ። በሐረርጌ ዞን በሸነን ዱጎ ወረዳ በማር ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንዳሉት፣ ባለፉት አመታት የተከናወኑ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች የደን መጠን እንዲጨምርና ምንጮች እንዲጎለብቱ አድርገዋል። ይህም ከመደበኛ የግብርና ስራቸው በተጓዳኝ ለንብ ማነብ ስራ ምቹ ሁኔታ የፈጠረ መሆኑን ነው የሚናገሩት። በወረዳው የመደ ጃለላ ቀበሌ አርሶ አደር የሆኑት አህመድ አብዱሌ ፤ ከአካባቢው ስምንት አርሶ አደሮች ጋር በማህበር በመደራጀት የማር ልማት ስራ ላይ መሰማራታቸውን ይገልፃሉ። በአሁኑ ወቅትም 24 ዘመናዊ የንብ ቀፎዎች እንዳሏቸው አመልክተው በዘርፉ በተሻለ መንገድ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወንም በግብርና ባለሙያዎች የቅርብ ክትትልና እገዛ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልጸዋል። አርሶ አደር መሐመድ አህመድ በበኩላቸው፤ በዘንድሮ ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ በንብ ማነብ ሥራ በመሰማራት የማር ልማት ስራ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም ከግብርና ባለሙያዎች በተደረገላቸው ድጋፍና ክትትል ከንብ ማነብ ሥራ ጎን ለጎን በወተት ላም እርባታ ላይ በመሰማራት ኑሯቸውን ለማሻሻል እየሰሩ መሆኑን ገልፀዋል። የመደ ጃለላ ቀበሌ ምክትል አስተዳዳሪ ወይዘሮ ፀሐይ እንግዳ እንዳሉት፤ ባለፉት አመታት የተካሔደው የአካባቢ ጥበቃና እንክብካቤ ስራ ለንብ ማነብ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል። በዋናነትም የደኖች መበራከትና የምንጮች መጎልበት በአካባቢው ለሚገኙ አርሶ አደሮች በተለያዩ የግብርና ልማት ስራዎች እንዲሳተፉ መነቃቃት የፈጠረ ነው ብለዋል። የአካባቢው አርሶ አደሮች ከመደበኛ የግብርና ስራቸው በተጓዳኝ በንብ ማነብ ስራ ላይ እንዲሰማሩና ውጤታማ እንዲሆኑ የባለሙያ ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው መሆኑን ተናግረዋል። በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ግብርና እና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ፅህፈት ቤት የማር ልማት ባለሙያ አቶ ከድር አደም እንዳሉት፤ በዞኑ ተግባራዊ የተደረገው የማር ልማት ኢኒሼቲቭ የምርታማነት መጠኑ በከፍተኛ ሁኔታ እንዲጨምር አድርጓል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ30ሺ በላይ ዘመናዊ ቀፎዎች ለአርሶ አደሩ የተሰራጨ ሲሆን ከ 4 ሺህ ቶን በላይ የማር ምርት መገኘቱን አመልክተዋል። በዚህ ዓመት የተገኘው ምርት መጠን ባለፈው ዓመት ከተገኘው ጋር ሲነፃፀር ከ500 ቶን በላይ ብልጫ እንዳለውም ጠቁመዋል፡ በአዲሱ በጀት ዓመትም የምርት መጠኑን በእጥፍ ለማሳደግ ከ60 ሺህ በላይ ዘመናዊ ቀፎዎችን ለማሰራጨት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። በዞኑ ከተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ጋር በተያያዘ ለንብ ማነብ ስራ አመቺ ሁኔታ መፈጠሩን የገለፁት ባለሙያው ከ150ሺ በላይ አርሶ አደሮችም በግልና በማህበር ተደራጅተው በንብ ማነብ ስራ ላይ መሳተፋቸውን አመልክተዋል።
የበና ፀማይ ወረዳ አርብቶ አደሮች በመስኖ ልማት ስራ ላይ በመሳተፍ ተጠቃሚ እየሆኑ ነው
Jul 22, 2026 284
ጂንካ፤ ሐምሌ 15/2018(ኢዜአ) :- በደቡብ ኦሞ ዞን በና ፀማይ ወረዳ በመስኖ ልማት ስራ ላይ በስፋት በመሳተፍ ተጠቃሚ መሆናቸውን የአካባቢው አርብቶ አደሮች ተናገሩ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኘው የደቡብ ኦሞ ዞን በቆላማነት ከሚጠቀሱ አከባቢዎች አንዱ በመሆኑ በተለይም የመስኖ ልማት ስራ ልዩ ትኩረት የተሰጠበት ስፍራ ሆኗል። በዚሁ መሰረትም አርሶና አርብቶ አደሮች የአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም የተለያዩ የግብርና ምርቶችን በስፋት በመስኖ ማምረታቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል። በዞኑ በና ፀማይ ወረዳ ከሚገኙት መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው አርብቶ አደሮች የመስኖ ልማት ስራ በስፋት በማከናወን ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። በወረዳው የጊስማ ባቦ ቀበሌ ነዋሪ ባካ ዋልታ፤ አከባቢው የዝናብ እጥረት ያለበት መሆኑን ታሳቢ በማድረግ በመንግሥት የተገነባው የመስኖ አውታር የእርሻ ስራው እንዲስፋፋ አድርጓል ብለዋል ። ከመስኖ ልማት በተጨማሪ በእንስሳት እርባታና ተያያዥ የግብርና ልማት ስራዎች ለራሳቸውና ለቤተሰባቸው በምግብ ራስን ለመቻል መብቃታቸውን ተናግረዋል። በወረዳው የዱማ ቀበሌ የሚኖረው ወጣት ሻዳ አይኬ በበኩሉ፤ በመንግሥት በተዘረጋው የመስኖ አውታር ተጠቅሞ ዘንድሮ በ1 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ላይ የተከለው ሽንኩርት ከፍተኛ ገቢ የሚጠብቅ መሆኑን ገልጿል። የመስኖ ልማትን በአግባቡ መጠቀም ከጀመረ ወዲህ በእርሱና ቤተሰቡ ላይ ለውጥና መሻሻል መኖሩን አንስቶ ስራውን አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ተናግሯል። በበና ፀማይ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት የግብርና ቴክኖሎጂ ኤክስቴንሽን ባለሙያ አንተነህ መኮንን፤ በወረዳው የአርብቶ አደሮችን የኑሮ ዘይቤ በማሻሻል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ጥረቶች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን ተናግረዋል። ከጂንካ ግብርና ምርምርና ከሌሎች ተቋማት ጋር በመቀናጀት 'ዊሊያም'' እና ''አምቦሀ'' በተባለው የተሻሻለ የሙዝ ዝርያን ጨምሮ የተሻሻሉ የሰብል፣ የሆርቲካልቸር ዝርያዎችን በማላመድ ለአርብቶ አደሩ የማሰራጨት ስራ እየተሰራ ይገኛልም ነው ያሉት። የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ ምንላርገው አዲሱ፤ በዞኑ ''ከተረጂነት ወደ ምርታማነት'' የሚለውን መርህ ተግባራዊ በማድረግ ምርታማነትን የማስፋትና የማሳደግ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። የአርብቶ አደሩን የመስኖ ልማት አጠቃቀም በማሳደግ፣ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማስፋት እና የሜካናይዜሽን እርሻን በማስፋፋት የአርብቶ አደሮችን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ከ55 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል
Jul 22, 2026 158
ባህር ዳር ፤ሐምሌ 15/2018( ኢዜአ)፡-በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ55 ሺህ በላይ ለሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር መቻሉን የከተማ አስተዳደሩ ስራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ዘመነ አሰፋ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በተጠናቀቀው በጀት አመት ለ45 ሺህ 300 ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ታቅዶ ከአቅድ በላይ ከ55 ሺህ የሚሆኑ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል። የስራ እድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች ውሰጥም ከ38 ሺህ በላይ ለሚሆኑት ቋሚ፣ቀሪዎቹ ደግሞ ጊዜያዊ የስራ እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የስራ እድሉ በውጭ ሀገር የስራ ስምሪት፣ በከተማ ግብርና፣ ማኑፋክቸሪንግ ፣ ኮንስትራክሽን፣ በአገልግሎትና ሌሎች ዘርፎች የተፈጠረ መሆኑን ተናገረዋል። በዚህ ወቅት ሦስት ሺህ 65 የሚደርሱ ኢንተርፕራይዞችን በማደራጀት ወደ ስራ ማስገባት የተቻለ መሆኑንም ነው ያስረዱት። ለስራ እድል ተጠቃሚዎች ከ321 ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆን መደበኛና ተዘዋዋሪ ብድር ማመቻቸት እንደተቻለም ነው የጠቀሱት። በተጨማሪም በ128 ሚሊዮን ብር ወጭ የስራ እድሉ ለተፈጠረላቸው ዜጎች የመስሪያ ማሽኖችን ማቅረብ መቻሉን ጠቁመው 125 ሼዶችና ኮንቴነሮችንም ማስተላለፍ መቻሉን አስገንዝበዋል። የስራ እድል ከተፈጠረላቸው መካከል ወይዘሮ እናንዬ ታምሩ እንደገለጹት፤ ከ40 በላይ ሴቶች በአንድ ላይ ተደራጅተን አሳ የማቅረብ ፣የማዘጋጀትና የማከፋፈል ስራ በመስራት ውጤታማ ሆነናል። የማህበሩ አባላትም ከሚያገኙት ገቢ ከእለት ፍጆታ ባለፈ የቁጠባ ባሕላቸውን ለማዳበር ያስቻላቸው በመሆኑም በዘርፉ በስፋት ወደ ስራ ለመግባት ጥረት እያደረጉ መሆኑን ነው የገለጹት። ሁለት ሆነው በመደራጀት በጀመሩት የልብስ ስፌት ስራ ውጤታማ በመሆኑ ተጨማሪ ማሽኖችን በመግዛት ለሌሎች ስራ ለመፍጠር ጥረት እያደረጉ መሆኑን የተናገረችው ደግሞ ወጣት እናኑ ደሴ ናት። አሁን ላይ በገቢም ሆነ በማምረት የተሻለ ቁመና ላይ እንገኛለን፤ለዚህም በከተማ አስተዳደሩ የተደረገልን ብድርና ሌሎች ድጋፎች ትልቁን ድርሻ ይወስዳል ብላለች።
በክልሉ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን በራስ አቅም ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም እየተገነባ ነው
Jul 22, 2026 146
ሐዋሳ፤ ሃምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን በራስ አቅም የተቀናጀና ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም እየተገነባ መሆኑን የክልሉ አደጋ ስጋት ስራ አመራርና የድጋፍ ማስተባበሪያ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ የሲዳማ ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራርና የድጋፍ ማስተባበሪያ ኮሚሽነር ሃይሉ ሃሰና፤ በክልሉ ለአደጋ ዝግጁ ከመሆንና ፈጣን ምላሽ ከመስጠት አንፃር እየተደረገ ያለውን ጥረት በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በማብራሪያቸውም በክልሉ ለአደጋ ጊዜ ዝግጁነትን ለማጠናከር ከሜቲዎሮሎጂ ኤጄንሲ፣ ከፌዴራል አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን እና ሌሎችም የሚመለከታቸው አካላት ጋር ጠንካራ ትብብር በመፍጠር እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም የምርት አቅምን በማሳደግ ለአደጋዎች ፈጣንና የተሟላ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል ዝግጅት ከማድረግ ባለፈ የቅድመ ማስጠንቀቂያና የግንዛቤ ፈጠራ ስራዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል ብለዋል። የዘንድሮው የበልግ ዝናብ በአንዳንድ አካባቢዎች በአግባቡ ያልተዳረሰ በመሆኑ በተለይም የበቆሎ ምርት ላይ ችግር በመፍጠሩ በአጭር ጊዜ የሚደርሱ ሰብሎችን በመዝራት ለማካካስ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ለምግብ እጥረት ተጋላጭ የሆኑ አካባቢዎችን በመለየትም በሌማት ትሩፋትና ሌሎችም የግብርና ኤንሸቲቮች ምርታማ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። የመጠባበቂያ እህል ክምችት አቅምን የማሳደግ እንዲሁም የሰብል ልማትና የመጠባበቂያ ፈንድ የማሰባሰብ ጥረት በተጠናከረ መልኩ መቀጠሉን ተናግረዋል። በሲዳማ ህዝብ ዘንድ በሚታወቀው ''ፎጮ'' የተሰኘ ባህላዊ ስርአት አማካኝነት ያለው ለሌለው እህል የማሰባሰብ ልምድም ተግባራዊ እየሆነ ነው ብለዋል። ለአደጋዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት ከ200 ሚሊየን ብር በላይ የመጠባበቂያ ፈንድ መኖሩን የጠቀሱት ኮሚሽነሩ በተያዘው ዓመትም ተጨማሪ የመጠባበቂያ ፈንድ የማሰባሰብ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ ተናግረዋል። እንደ አጠቃላይ በሲዳማ ክልል የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን በራስ አቅም የተቀናጀና ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም እየተገነባ ይገኛል ብለዋል። በባለፈው ክረምት የወንዝ ሙላት፣ ጎርፍና የመሬት መንሸራተት ያስከተለውን አደጋ መነሻ በማድረግ ለተመሳሳይ አደጋዎች በስጋት አካባቢ የሚኖሩ ወገኖችን ወደ ሌሎች አካባቢዎች የማስፈር ስራ መሰራቱን አንስተዋል።
በዞኑ ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመኸር አዝመራ እየለማ ነው
Jul 21, 2026 286
አምቦ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፡-በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመኸር አዝመራ እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ፡፡ በዞኑ ኢልፈታ ወረዳ በመኸር አዝመራ በኩታ ገጠም 1 ሺህ 300 ሄክታር መሬት ላይ የቢራ ገብስ ዘር የመዝራት መርሃ ግብር የዞኑና የወረዳው የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ተካሂዷል፡፡ የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ መርጋ አየለ እንደገለጹት፤ በመኸር እርሻው ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር የመሸፈን ሥራ እየተከናወነ ይገኛል፡፡ በመኸር አዝመራው በቆሎ፣ ገብስ፣ ማሽላ እና ስንዴ በኩታ ገጠም የሚለሙ ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ ከ48 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቢራ ገብስ ለማልማት ታቅዶ እስካሁን 22 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በዘር መሸፈኑን ተናግረዋል። በምርት ዘመኑ የተሻለ ምርት ለማግኘት በአሲድ የተጠቃን መሬት በኖራ በማከም፣ እንዲሁም ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሮች በስፋት እየቀረበ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የኢልፈታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ፈይሳ ቶለሳ በበኩላቸው፤ የወረዳው አርሶ አደሮች የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴን እየተላመዱ መምጣታቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ምርትና ምርታማነት እያደገ መምጣቱን ጠቁመው፤ በዘንድሮው የመኸር እርሻ በወረዳው 32 ሺህ 932 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህ ውስጥ 2 ሺህ 960 ሄክታር መሬት በቢራ ገብስ ለማልማት የታቀደ ሲሆን፣ እስካሁን በተከናወኑ ሥራዎች 83 በመቶ የሚሆነው በዘር መሸፈኑን አስረድተዋል። የወረዳው አርሶ አደሮች በበኩላቸው፣ በግብርና ጽሕፈት ቤቱ በተደረገላቸው ድጋፍ የቢራ ገብስን በኩታ ገጠም ማልማት ከጀመሩ ወዲህ ገቢያቸው ማደጉን በመግለጽ ምርታቸውን ለማሳደግም ጥረት እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። አርሶ አደር ለሊሳ ገላና፤ ገብስን ቀደም ሲል በኩታ ገጠም ማረስ ሳይጀምሩ ከአንድ ሄክታር 15 ኩንታል ምርት ብቻ ያገኙ እንደነበር አብራርተው፣ አሁን ላይ የግብርና ባለሙያዎች የሚያደርጉላቸውን ድጋፍ ተጠቅመው ከአንድ ሄክታር እስከ 50 ኩንታል ምርት ለማግኘት እየሠሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ሌላው አርሶ አደር ኢትሳ ጃለታ፤ ገብስን በኩታ ገጠም ማረስ ከጀመሩ ሶስት ዓመት እንደሆናቸው ጠቅሰው፣ ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ ስለሚያገኙ ምርታቸው እያደገ መምጣቱንና ዘንድሮም ከልማቱ ተጠቃሚ ለመሆን መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።