ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በተቀናጀ ዐቅም ተግተን ከሠራን ብልጽግና ሕይወት፣ድህነት ታሪክ ይሆናል- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Aug 16, 2026 94
አዲስ አበባ ፤ነሀሴ 10 /2018 (ኢዜአ)፦ለም አፈር፣ ንጹሕ ውኃና ሥራ ወዳድ ሕዝብ ባለበት ምድር፣ በተቀናጀ ዐቅም ተግተን ከሠራን ብልጽግና ሕይወት፣ ድህነት ታሪክ ይሆናል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለፁ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልእክት የሃይቅ ዙሪያ አርሷደሮች መሬት እና እርሻቸውን ከጫት ወደ አትክልት እና ፍራፍሬ ክላስተር አሸጋግረውታል ብለዋል። አርሷደሮቹ የአካባቢን አንጻራዊ የልማት ጉልበት መለየት እና ወደ አትራፊ እና ዘላቂ የግብርና ጎዳና መሸጋገር ይገባል የሚለውን ሃገራዊ መርህ እና ስምሪት ተግብረው አሳይተዋል ነው ያሉት። ከዚህ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ምርቃት ላይ ባስተላለፉት ታሪካዊ መልዕክት "ሐይቅ የታሪክ ብቻ ሳይሆን የፍራፍሬ ልማት፣ የተትረፈረፈ ምርት፣ የውበትና የጥጋብ ሥፍራ መሆን አለባት" ማለታቸውን አስታውሰዋል። ዛሬ የርሳቸው ቃል ፍሬ አፍርቶ በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን፣ ተሁለደሬ ወረዳ የጎበያ ቀበሌ በአትክልት እና ፍራፍሬ ክላስተር ተሸፍኗል። ይህ የልማት ትጋት ኢትዮጵያ ለጀመረችው የምግብ ሉዓላዊነት ተደማሪ ጥሪት እና ወረት ነው ሲሉ ጠቁመዋል። መንግሥት ለዚህ ልማት አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረጉን ይቀጥላል ያሉ ሲሆን ለም አፈር፣ ንጹሕ ውኃና ሥራ ወዳድ ሕዝብ ባለበት ምድር፣ በተቀናጀ ዐቅም ተግተን ከሠራን - ብልጽግና ሕይወት፣ ድህነት ታሪክ እንደሚሆን ገልጸዋል።
በአማራ ክልል የሚገኙ ከተሞችን በፕላን ለመምራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው-ኢንስቲትዩቱ 
Aug 16, 2026 112
ጎንደር ፤ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የሚገኙ ከተሞችን ዘላቂ ልማት ለማረጋገጥ የሚያስችል ፕላን ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ፕላን ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ያለፈው ዓመት አፈጻጸም፣ የ2019 ዕቅድ ትውውቅና የተለያዩ የሕግ ማዕቀፎችን መሠረት ያደረገ የውይይት መድረክ በጎንደር ከተማ እያካሄደ ነው።   በውይይቱ ላይ የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዳይሬክተር ተስፋሁን ተናኜ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ከተሞች ለነዋሪዎቻቸው ምቹ፣ ተወዳዳሪና ዘላቂ ልማት የሚያረጋግጡ እንዲሆኑ እየተደረገ ነው። ከዚህ ውስጥም የከተሞችን ዕድገት ለማፋጠን በየደረጃው መዋቅራዊ ፕላን በማዘጋጀት እስካሁን ከ137 በላይ ለሚሆኑ ከተሞች የፕላን ዝግጅት ተከናውኗል። በተጨማሪም፣ ከ31 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የግንባታ ጥያቄዎች በከተሞች ፕላን መሠረት መከናወናቸውን ማረጋገጥ ተችሏል። ይህም በከተሞች የመንገድ፣ የውኃ፣ የመብራትና ቴሌኮም የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እንዲሳለጡ የሚያደርግ መሆኑን አስገንዝበዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም የተጀመሩ ተግባራትን በማጠናከር፣ የከተሞችን ዕድገትና ዘመናዊነት የሚያረጋግጡ ዕቅዶች ተግባራዊ ይደረጋሉ ነው ያሉት። በክልሉ ፕላን ኢንስቲትዩት የጎንደር ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ግዛቸው አዳነ በበኩላቸው፣ የከተሞች ፕላን ክለሳ፣ የመዋቅራዊና መሠረታዊ ፕላን ዝግጅት እና የሰፈር ልማት ፕላን ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቱ በማዕከላዊ ጎንደር፣ በምዕራብ ጎንደር እና በሰሜን ጎንደር ዞኖች ሥር የሚገኙ ከተሞችን በመከታተል የፕላን ዝግጅትና ትግበራ ድጋፍ እያደረገ ነው ብለዋል። ከዛሬ ጀምሮ ለሦስት ቀናት በሚካሄደው በዚህ መድረክ ላይ የኢንስቲትዩቱ የሥራ ኃላፊዎችና የቅርንጫፍ አመራሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።  
የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተተገበሩ የፖሊሲ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው - ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር)
Aug 16, 2026 187
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፦የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተተገበሩ የፖሊሲ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የግብርናውን ዘርፍ ውጤታማነት ለማሳደግ ተግባራዊ የተደረጉ የፖሊሲ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤቶች እያመጡ ነው። የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል የተመቻቹ የፋይናንስ አቅርቦት ዕድሎች የግል ባለሀብቶችን ተሳትፎ እያሳደጉ መምጣታቸውንም ገልጸዋል። ይህም የግሉ ዘርፍ በፋይናንስ፣ በቴክኖሎጂና በሌሎች የትብብር መስኮች የሚያደርገውን ተሳትፎ ለማጎልበት ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊ የግብርና ግብዓቶችና ሜካናይዜሽን በሰፊው ጥቅም ላይ እንዲውሉ መደላድል በመፈጠሩም የምርት መጠንና ጥራት እያደገ መምጣቱን አስረድተዋል። የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥም በማዳበሪያ አቅርቦት ላይ ያለውን ጥገኝነት በሀገር ውስጥ አቅም ለመተካት የሚያስችል የማዳበሪያ ፋብሪካ በግንባታ ሂደት ላይ መሆኑን አንስተዋል።   የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአምስት ዓመታት ጊዜ የታረሰውን መሬት በሦስት እጥፍ ማሳደግ እንደተቻለ አስረድተዋል። በዚህም በሰብልና በእንስሳት ሃብት ልማት ምርታማነትን ጨምሮ በሁሉም የግብርና ዘርፎች የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል እምርታዊ ዕድገት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል። የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥም ከሀገር ነፃነትና ደህንነት ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት ያለው ቁልፍ ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ ዐሻራ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቀነስ ለግብርና ምርታማነት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እያስገኘ ነው ብለዋል። ይህም የግብርናውን ትራንስፎርሜሽን ውጤታማነት በማጎልበት የምግብ ዋስትና እንዲረጋገጥ መሠረት ከመጣል ባሻገር በሥራ ዕድል ፈጠራም የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩ የሀገር ውስጥ ፍጆታን ከመሸፈን ባለፈ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶች እየተገኙበት ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታዋ፤ የውጭ ምንዛሬ ግኝትም እንዲጨምር እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አረንጓዴ ዐሻራ የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በማስጠበቅ በካርቦን ሽያጭ ጭምር ገቢ መፍጠር እያስቻለ ነው ብለዋል። ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ሥርዓት ለመገንባት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑንም ገልጸዋል።  
የአዲስ አበባን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የፍሳሽ ማጣሪያ አቅም የሚያጎለብት ውጤታማ ሥራ እየተሠራ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Aug 16, 2026 168
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የፍሳሽ ማጣሪያ አቅም የሚያጎለብት ውጤታማ ሥራ እየተሠራ መሆኑን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአራብሳ አካባቢ የተገነባውን የንጹህ መጠጥ ውሃ መሠረተ ልማትና የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።   ከንቲባዋ በዚሁ ወቅት፣ ፕሮጀክቱ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትን በጉልህ እንደሚያሳድግ ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት የንጹህ የመጠጥ ውሃ እጥረትን ለመፍታት የተከናወኑ ሥራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ የመዲናዋ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት በቀን ከ910 ሺህ ሜትር ኪዩብ በላይ መድረሱን አስታውቀዋል። በቀጣይም ከፍተኛ የማምረት አቅም ያላቸው የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ እንደሚገቡ ተናግረዋል። በሌላ በኩል የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ የሕብረተሰቡን ጤናና የአካባቢ ጥበቃን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ከንቲባዋ ገልጸዋል። ጣቢያው ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም መሆኑን በማንሳት፣ መሰል የፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያዎችን በስፋት ለመገንባት መታቀዱን አስረድተዋል። መሠረተ ልማት መገንባት ብቻውን ግብ አይደለም ያሉት ከንቲባ አዳነች፤ የተገነቡትን መሠረተ ልማቶች መጠበቅና መንከባከብ የሁሉም የጋራ ኃላፊነት ሊሆን እንደሚገባ አስገንዝበዋል። አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ከተማ ለማድረግ የተጀመሩት የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በማንሳት፣ ለፕሮጀክቶቹ እውን መሆን አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል።   የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ዘሪሁን አባተ በበኩላቸው፤ የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ በቀን 20 ሺህ ሜትር ኪዩብ የማጣራት አቅም እንዳለው ገልጸዋል። ጣቢያው የከተማዋን የፍሳሽ ማጣራት አቅም በከፍተኛ ሁኔታ የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል። የከተማዋን እድገት የሚመጥኑ የመጠጥ ውሃና የፍሳሽ ማጣሪያዎች በተለያዩ አካባቢዎች እየተገነቡ መሆናቸውን አንስተዋል። የዛሬው ቀን የፕሮጀክት መጠናቀቅን ብቻ የሚያሳይ አይደለም ያሉት ደግሞ በአለም ባንክ ምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሪጅን፣ የኢትዮጵያ፣የሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን እና ኤርትራ ተወካይ ዲቪዥን ዳይሬክተር ራጁል አዋስቲ ናቸው።   የኮዬ የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ጣቢያ አዲስ አበባ ንፁህ፣ ጤናማ እና የተሻለች ከተማ ለመሆን የምታደርገው ጉዞ ታሪካዊ ምዕራፍ መሆኑን ጠቁመዋል። የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ የከተሞች የውሃ እና ሳኒቴሽን ዘርፍ የሚያደርገው ተሳትፎ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለውን የረጅም ጊዜ እና ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠውን አጋርነት የሚያንጸባርቅ መሆኑን ተናግረዋል።  
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ተጨማሪ ሃብት ለማፍራት አስችሎናል-ተጠቃሚዎች
Aug 16, 2026 143
ጎንደር፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ) ፡-የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ኑሯቸውን ለመለወጥና ተጨማሪ ሀብት ለማፍራት እንዳስቻላቸው በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ተጠቃሚዎች ገለጹ። የሌማት ትሩፋት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የሥነ-ምግብ ደረጃን ለማሻሻልና አጠቃላይ የግብርና ምርታማነትን በጥራትና በብዛት ለማሳደግ ያለመ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው። መርሃ-ግብሩ በተለይም በወተት፣ በማር፣ በዶሮ እርባታ፣ በሥጋ እንዲሁም በጓሮ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ላይ ትኩረት በማድረግ የቤተሰብ ገቢን ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። በወገራ ወረዳ አምባ ጊዮርጊስ ከተማ በዶሮ እርባታ ሥራ የተሰማሩት አቶ አበራ ምስጋናው ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር በመታቀፍ በ1 ሺህ ጫጩቶች የጀመሩትን ሥራ በርትተው በመስራት የተሻለ ገቢ ማግኘት ጀምረዋል።   ሥራቸውን በማስፋፋትም አሁን ላይ በአንድ ጊዜ እስከ 3 ሺህ የሚደርሱ ዶሮዎችን አሳድገው ለመሸጥ የሚያስችል አቅም መፍጠራቸውን ተናግረዋል። ሌላው የከተማዋ የ02 ቀበሌ ነዋሪ አቶ ማርየ ራራ በበኩላቸው፤ ከመንግሥት ሥራቸው ጎን ለጎን ባላቸው ትርፍ ጊዜ በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር መሳተፋቸው የቤተሰባቸውን ሕይወት ከመለወጡ ባለፈ ተጨማሪ ሀብት ለመፍጠር እንደቻሉ ተናግረዋል።   አስተያየት ሰጪዎቹ በተሰማሩበት የዶሮ እርባታ ሥራ ውጤታማ እንዲሆኑ ከአካባቢው አስተዳደር የተደረገላቸው የቦታና የብድር ድጋፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አብራርተዋል። የማዕከላዊ ጎንደር ዞን የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ ዶክተር ምስጋናው ታከለ በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ብቻ ለ20 ሺህ 588 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ተናግረዋል።   ዘርፉ ሥርዓተ-ምግብን ከማሻሻል ባለፈ ዜጎች የኑሮ ሁኔታቸውን እንዲለውጡና ሀብት እንዲፈጥሩ ማስቻሉንም አስረድተዋል።  
ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል የመንግስትና የህዝብ ሀብትን ከብክነት ማዳን ተችሏል
Aug 16, 2026 146
አዳማ፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፡- ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል የመንግስትና የህዝብ ሀብትን ከብክነት ማዳን መቻሉን የአዲስ አበባና የድሬዳዋ አስተዳደር ሥነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች አስታወቁ። የፌዴራል ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ያዘጋጀው 17ኛው ሀገር አቀፍ የሥነ-ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች ትስስር ጉባኤ ትናንት በአዳማ ከተማ ተካሂዷል። የአዲስ አበባ ከተማ ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽነር ጀማል ረዲ በዚሁ ወቅት ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል የመንግስትና የህዝብ ሀብትን ከብክነት ለማዳን ሰፋፊ ስራዎች ተከናውነዋል። ከዚህ ውስጥም ኮሚሽኑ በአስቸኳይ ሙስና መከላከል የሥራ ዘርፍ ከሕዝብ የቀረቡለትን 290 ጥቆማዎች ተቀብሎ በመመርመር፣ 80 በመቶ የሚሆኑት የሙስና ይዘት እንዳላቸው ማረጋገጡን ገልጸዋል። ይህንን ተከትሎ በተወሰደው እርምጃ በአስቸኳይና በመደበኛ ሙስና መከላከል ተግባራት በአጠቃላይ ከ706 ሚሊዮን ብር በላይ ከምዝበራ ማዳን ተችሏል ነው ያሉት። ከገንዘብ በተጨማሪም 8 ሺህ 103 ካሬ ሜትር መሬት በማዳን ወደ መሬት ባንክ ገቢ እንዲሆን መደረጉን ተናግረዋል። ብልሹ አሰራሮችንና ሙስናን የመከላከል እርምጃዎችን ለማጠናከር የጥቆማ ሥርዓቱ ዘመናዊና ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን የጥሪ ማዕከል የማደራጀት እና ጥቆማዎች በዘመናዊ ዳታቤዝ እንዲያዙ የማድረግ ስራ መሰራቱን ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ በመዲናዋ በበጀት ዓመቱ በትውልድ ሥነ-ምግባር ግንባታና በሙስና መከላከል በኩል ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቁመዋል። በተለይም የፀረ-ሙስና ትግሉን ከማጎልበት አንጻር የተለያዩ መድረኮችን በማዘጋጀት ለ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን የኅብረተሰብ ክፍሎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና መሰጠቱን አስታውቀዋል።   የድሬዳዋ አስተዳደር የሥነ-ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽነር አቶ ፌኑስ አብዱልጀባር በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተለያዩ ተቋማት ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከል የሚያስችል ጥናት መካሄዱን ገልጸዋል። በተለይም በአስቸኳይ ሙስና መከላከል በተደረገው ጥረት በድሬዳዋ አስተዳደር ድሬ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ፤ የፔዳጎጂካል ቴክኖሎጂ፣ ኮምፒዩተር እና ተያያዥ አክሰሰሪዎች ግዥ ጨረታ ግልጽነት የጎደለው ሆኖ መገኘቱን ለአብነት አንስተዋል። የግዥ ጨረታው ህጋዊ አሰራርን ያልተከተለና ውስንነት ያለበት በመሆኑም ሂደቱ ተቋርጦ፣ ተስተካክሎና ህጋዊ አሰራርን ተከትሎ እንዲቀጥል መደረጉን ተናግረዋል። አስተዳደሩ የሙስና ትግሉን ህዝባዊ መሰረት ለማስያዝ በተለያዩ አማራጮች ግንዛቤ ለመፍጠር እየሰራ መሆኑን አመልክተው፤ ህብረተሰቡ ሙስና እና ብልሹ አሰራርን ሲመለከት ጥቆማ በመስጠት ረገድ የተሻለ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው ብለዋል።  
በአፋር ክልል የገቢ አማራጮችን የማስፋትና በቁርጠኝነት ገቢን የመሰብሰብ ተግባራት ይጠናከራሉ
Aug 16, 2026 103
ሰመራ፣ነሀሴ 10/2018 (ኢዜአ):- በአፋር ክልል በተያዘው በጀት ዓመት የገቢ አማራጮችን የማስፋትና በቁርጠኝነት ገቢን የመሰብሰብ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ ገለጹ። የተጠናቀቀው በጀት ዓመት አፈፃፀምና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ የሥራ ኃላፊዎች የተገኙበት የውይይት መድረክ በሰመራ ተካሄዷል።   በውይይት መድረኩ ማጠቃለያ ላይ የተገኙት ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እንደተናገሩት፣ የክልሉን ልማት ለማቀላጠፍና የህብረተሰብ ጥያቄዎችን ለመመለስ ገቢን በአግባቡ መሰብሰብ ከፍተኛ ሚና አለው። ርዕሰ መስተዳድሩ አክለውም፣ በተያዘው በጀት ዓመት በክልሉ የገቢ አማራጮችን የማስፋትና በቁርጠኝነት ገቢን የመሰብሰብ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። ከዓመት ወደ ዓመት ገቢን የመሰብሰብ አቅም እየጨመረ መምጣቱን ገልጸው፣ ከለውጡ በፊት የነበረውን 790 ሚሊዮን ብር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ወደ 8 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል። የመሰብሰብ አቅምን በማሳደግ በጀትን በራስ አቅም ለመሸፈን የሚደረገው ጥረት እየተጠናከረ መምጣቱን ገልጸው፣ በተለይም አመራሩ ኃላፊነቱን በአግባቡ ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል። መተባበርንና መትጋትን ማዕከል በማድረግ የታቀደውን ዕቅድ ለማሳካት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አብራርተዋል። በያዝነው ዓመት ደግሞ የገቢ ግብርን ከፍ በማድረግ ከ16 ቢሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ የተገባ መሆኑን ገልጸው፣ ለዚህ ስራ ስኬታማነት በየደረጃው ያለው አመራር የድርሻውን መወጣት እንዳለበትም አስገንዝበዋል። በተያዘው በጀት ዓመት ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ ለሕዝብ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ የመስጠቱ ተግባርን ማጠናከር ከሁላችንም ይጠበቃል ያሉት ደግሞ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ አወል አብዱ ናቸው። የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር አህመድ ኑር ሳሊም በበኩላቸው፣ የከተማዋን የገቢ አቅም የመለየት ስራዎች መከናወናቸውንና ለፈጻሚ ባለሙያዎች ትጥቅ የሚሆናቸው ስልጠናና የልምድ ልውውጥ መካሄዱንም በመድረኩ ገልጸዋል።   በመርሃ ግብሩ ማጠቃለያ ላይ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ የተሻለ አፈፃፀም ላስመዘገቡ ከተማ አስተዳደሮችና ወረዳዎች የእውቅና እና የሽልማት ስነ-ስርዓት አከናውነዋል።        
የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ልማት ዕድገትን የሚያፋጥን አስደማሚ ውጤት እያመጣ ነው - ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ምሁራን
Aug 16, 2026 226
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 10/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ልማት ዕድገትን የሚያፋጥን አስደማሚ ውጤት እያመጣ መሆኑን የአሜሪካ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ምሁራን ገለጹ። አሜሪካዊው ፕሮፌሰር ኤድዋርድ ሚጉኤል እና ካሜሩናዊው የኢኮኖሚክስ ፕሮፌሰር ሊነስ ኒውል ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በተለያዩ ዘርፎች አስደናቂ ዕድገትና ለውጥ አስመዝግባለች። በአሜሪካ የካሊፎርኒያ በርክሌይ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ ፕሮፌሰር ኤድዋርድ ሚጉኤል፣ ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ሲመለሱ በአዲስ አበባ የተመለከቱት ለውጥ እጅግ የሚያስደምም መሆኑን ገልጸዋል። የአዲስ አበባ አስደናቂ የከተሜነት ዕድገትና የልማት ለውጥ ከዚህ ቀደም ያውቋቸው የነበሩ አካባቢዎችን ገጽታ በእጅጉ በመቀየሩ እንደገና ለመለየት እንኳን እንደተቸገሩ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት ለከተማ መሠረተ ልማት የሰጠው ልዩ ትኩረት የኢኮኖሚ ዕድገትን በማፋጠን መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑንም ገልጸዋል። በከተማ ልማት፣ በኢኮኖሚ ማሻሻያና በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም የተመዘገቡ ውጤቶች የኢትዮጵያን የልማት ቁርጠኝነት የሚያሳዩ አስደናቂ ስኬቶች መሆናቸውን አንስተዋል። ኢትዮጵያ በብዝኅ ኢኮኖሚ ዘርፎች የወሰደቻቸው የፖሊሲ ማሻሻያ እርምጃዎችም ዕድገትን በማፋጠን አዎንታዊ ውጤት እያመጡ እንደሚገኙ አንስተዋል። በአየር ንብረት ለውጥ ረገድም ኢትዮጵያ አዳዲስ የማኅበራዊ ፕሮግራሞችንና የፋይናንስ አሠራሮችን በመዘርጋት የመቋቋም አቅሟን ለማሳደግ የወሰደቻቸው እርምጃዎች የሚደነቁ መሆናቸውን ጠቁመዋል። አፍሪካ ለድርቅና ለጎርፍ ተጋላጭ በሆነችበት በዚህ ወቅት የመንግሥት ቁርጠኝነትና በዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ ጥረቶች እጅግ አስፈላጊ መሆናቸውንም አብራርተዋል።   በአሜሪካ ፔንሲልቬኒያ ጌቲስበርግ ኮሌጅ የኢኮኖሚክስ ምሁር የሆኑት ካሜሩናዊው ፕሮፌሰር ሊነስ ኒውል በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች አስደናቂ ዕድገት እያስመዘገበች መሆኑን ገልጸዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የወሰደቻቸው አስደናቂ የልማት መርሃ ግብሮችም የሀገሪቱን ዕድገት ከማፋጠን ባሻገር አረንጓዴ የኢኮኖሚ አቅሞችን ለመገንባት የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚን በመገንባት እያስመዘገበች ያለችው እመርታም ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጭምር የሚተርፉ ወሳኝ ተሞክሮ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያ መንግሥት በአየር ንብረት ለውጥ መከላከልና መቋቋም ውጤታማነቱን በማሳደግ፣ አህጉራዊ የምሪት ሚናዋን አጠናክራ ልትቀጥል እንደሚገባ አስገንዝበዋል።  
አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Aug 16, 2026 183
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 10/2018(ኢዜአ)፦አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአራብሳ አካባቢ የተገነባውን የንጹህ መጠጥ ውሃ መሠረተ ልማትና የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ከንቲባዋ በመርሃ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፣ ፕሮጀክቱ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትን በጉልህ እንደሚያሳድግ ገልጸዋል።   ባለፉት ዓመታት የመጠጥ ውሃ እጥረትን ለመፍታት የተከናወኑ ሥራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ጠቅሰው፣የመዲናዋ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት በቀን ከ910 ሺህ ሜትር ኪዩብ በላይ መድረሱን አስታውቀዋል። በቀጣይም ከፍተኛ የማምረት አቅም ያላቸው የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ እንደሚገቡ ተናግረዋል። በሌላ በኩል የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ የሕብረተሰቡን ጤናና የአካባቢ ጥበቃን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ከንቲባዋ ገልጸዋል። ጣቢያው ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም መሆኑን በማንሳት፣ መሰል የፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያዎችን በስፋት ለመገንባት መታቀዱን አስረድተዋል። መሠረተ ልማት መገንባት ብቻውን ግብ አይደለም ያሉት ከንቲባ አዳነች፣ የተገነቡትን መሠረተ ልማቶች መጠበቅና መንከባከብ የሁሉም የጋራ ኃላፊነት ሊሆን እንደሚገባ አስገንዝበዋል። አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ከተማ ለማድረግ የተጀመሩት የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በማንሳት፣ ለፕሮጀክቶቹ እውን መሆን አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በቀን 20 ሺህ ሜትር ኪዮብ ፍሳሽ የሚያጣራውን የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ ፕሮጀክት አስመረቁ
Aug 16, 2026 160
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 10/2018(ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በቀን 60 ሺህ ሜትር ኪዮብ ንፁህ የመጠጥ ውሃ የሚያመርት እና በቀን 20 ሺህ ሜትር ኪዮብ ፍሳሽ የሚያጣራ የኮዬ ፍሳሽ ዘመናዊ ማጣሪያ ጣቢያ ፕሮጀክቶችን አስመርቀው አገልግሎት አስጀምረዋል። ንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ለማሳደግ በቱሉ ጉዶ፣ ለገዳዲ ክፍል 2፣ በረከት የጋራ መኖሪያ አካባቢ፣ ቦሌ አራብሳና ሌሎችም በርካታ ጉድጓዶችን በማልማት በከተማዋ ከአምስት ዓመት በፊት የነበረው 525 ሺህ ሜትር ኪዩብ በቀን የማምረት አቅም ዛሬ ላይ 910 ሺህ ሜትር ኪዩብ መድረሱን በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ጠቁመዋል፡፡   ፕሮጀክቶቹ የነዋሪዎቻችንን ጤናና ንጽህና የሚጠብቁ፣ የወንዞቻችንን ብክለት የሚቀንሱ፣ የአካባቢ ጥበቃችንን የሚያጠናክሩ ናቸው ብለዋል። አዲስ አበባን እንደ ስሟ አዲስ ውብ፣ ጽዱ፣ ጤናማ፣ አረንጓዴ፣ ዘመናዊና ለትውልድ የምትመች ከተማ ለማድረግ የጀመረው ግብ ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት።   ይህ ታላቅ ፕሮጀክት እውን እንዲሆን የብድር አገልግሎት ለሰጠው የዓለም ባንክ፣ እንዲሁም የውሃው መገኛ አካባቢዎችን በትብብር ለማልማት ላገዘው የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልል፣ ከሁሉ በላይ ዘላቂ ኑሯቸውን ሲመሩበት የነበረውን መሬት ለዚህ ታላቅ ልማት የለቀቁ አርሶ አደሮች እና ለፕሮጀክቱ ስኬት ሌት ተቀን ያለእረፍት የተጉ የውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን አመራሮች እና ባለሙያዎች ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
የአቮካዶ ልማትን በማዘመን ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል- ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር
Aug 16, 2026 228
ሐረር፣ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፡- የአቮካዶ ልማትን በማዘመን ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ትኩረት መደረጉን የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድ ሮዛ ኡመር ገለጹ። ሀገር አቀፍ የአቮካዶ ልማት ኢኒሼቲቭ ከሚተገበርባቸው 10 ክልሎች መካከል አንዱ የሐረሪ ክልል ሲሆን በዛሬው እለትም በገጠርና በከተማ ክላስተሮች የአቮካዶ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ተከናውኗል።   የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ ኡመር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የክልሉ መንግሥት በርካታ ኢኒሼቲቮችን ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ ነው። በአሁኑ ወቅትም አቮካዶን ጨምሮ ሌሎች የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሥራዎችን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ሰፊ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልፀዋል። የአቮካዶ ልማት ኢኒሼቲቭ ዋና ዓላማ ምርቱን በቴክኖሎጂ በማዘመን አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ከማድረግ ባሻገር ምርቱን ለውጭ ገበያ ማቅረብን ጨምሮ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥና የሥራ ዕድል መፍጠር ነው ብለዋል።   በተለይ የክልሉ የአየር ፀባይ ለአቮካዶ ልማት ምቹ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በክልሉ የግብርና ልማት ቢሮ የብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ መሐመድ ሬድዋን ናቸው። በችግኝ ጣቢያዎች 106 ሺህ የተሻሻሉ የአቮካዶ ዝርያዎችን የማዘጋጀት ሥራ የተከናወነ ሲሆን፣ ችግኞቹን በገጠርና በከተማ በ100 ሄክታር መሬት ላይ ለማልማት መታቀዱን ገልጸዋል።   በችግኝ ተከላው ከተሳተፉት መካከል ወጣት ማሩፋ ሙሳ እና አርሶ አደር አብዲ በያን ፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የፍራፍሬ ችግኝ ተከላ ያስገኝውን ውጤት መነሻ በማድረግ አቮካዶን ይበልጥ ለማልማት መነሳሳታቸውን ነው የተናገሩት። አቮካዶ ልማት ሥራ ተጠቃሚነትን ከማጎልበቱ ባሻገር የሥራ ዕድል የሚፈጥር በመሆኑ በስፋት እየተሳተፉ እንደሚገኙም ነው ያመለከቱት።
በምዕራብ ጎንደር ዞን ከ172 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰሊጥና ማሾ ሰብል ለምቷል
Aug 16, 2026 89
ገንዳ ውኃ፣ ነሐሴ10/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን በመኸር እርሻ ከ172 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የሰሊጥና ማሾ ሰብሎችን ማልማት መቻሉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። ​የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የመምሪያው ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ዞኑ ለወጪ ንግድና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ የግብርና ምርቶችን በማምረት ላይ ይገኛል። በዚህም እስካሁን በተደረገው ጥረት በአጠቃላይ በሰሊጥና በማሾ ሰብል ከለማው ከ172 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ ከ169 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በሰሊጥ፣ ቀሪው ደግሞ በማሾ ሰብል መሸፈኑን ተናግረዋል።   ከዚህ ልማትም ከአንድ ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስረድተዋል። ምርታማነቱን ለማሳደግም ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘርና የመካናይዜሽን አስተራረስ ዘዴዎችን በመጠቀም መዝራት መቻሉን ጠቁመዋል። በሰብል ልማቱ ከ59 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችና 500 የሚደርሱ ባለሀብቶች እየተሳተፉ መሆናቸውን ገልጸው፣ የአረምና የተባይ መከላከል ተግባራት በቅንጅት እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። ጥራቱን የጠበቀ ምርት ለገበያ ለማቅረብም በቅድመና ድህረ-ምርት አያያዝ ላይ ተገቢው ክትትልና ቁጥጥር እንደሚደረግ አብራርተዋል። በዞኑ የመተማ ወረዳ አርሶ አደር አቶ መሐመድ አህመድ በበኩላቸው፣ ዝናብ ዘግይቶ ቢጥልም የተገኘውን እርጥበት በመጠቀም አራት ሄክታር መሬታቸውን በሰሊጥ መሸፈናቸውን ተናግረዋል። በኩታ ገጠም አስተራረስና በዘመናዊ መካናይዜሽን ተጠቅመው ካለሙት ሰብልም ከ30 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። ሌላው የመተማ ወረዳ አርሶ አደር ደሳለኝ ገብሬ፣ በዘንድሮው የመኸር እርሻ የግብዓት አቅርቦት በወቅቱ መድረሱ ማሾና ሰሊጥን በስፋት ለማልማት መቻላቸውን ገልጸዋል። አሁንም ዋና ትኩረታቸው ሰብሉን ከተባይ መጠበቅና ምርቱን ከብክነት በጸዳ መልኩ ሰብስቦ ለገበያ ማቅረብ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ ባለፈው የምርት ዘመን ከ163 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰሊጥ ሰብል ለምቶ ከ900 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
በሰሜን ሸዋ ዞን 543 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በመኸር እርሻ ለማልማት ተችሏል
Aug 16, 2026 164
ደብረ ብርሃን፤ ነሃሴ 10/2018(ኢዜአ)፡- በሰሜን ሸዋ ዞን በመኸር እርሻ 543 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት የእንክብካቤ ስራ እየተካሄደ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ ተውልኝ ሽባባው ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክረምቱ ወቅት በአጠቃላይ 563 ሺህ 043 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል።   እስካሁን በተደረገ ጥረትም 542 ሺህ 960 ሄክታር መሬት በዘር መሸፈን ተችሏል። ከ332 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የተካሄደው የዘር ስራ ከእቅዱ ጋር ሲነጻጸር ከ96 በመቶ በላይ መሳካቱን ተናግረዋል። በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥም 288 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በጤፍ፣ ስንዴ፣ ባቄላና ማሾ ሰብሎች በኩታ ገጠም የአሰራር ዘዴ የለማ መሆኑን ባለሙያው አረጋግጠዋል። ዝናብ ዘግይቶ ቢጥልም፣ በግብርና ባለሙያዎች የተጠናከረ ድጋፍ አርሶ አደሩ ሌት ተቀን እንዲረባረብ በማድረግ የተሻለ አፈፃፀም ማስመዝገብ ተችሏል ብለዋል። ምርታማነትን ለማሳደግም 720 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ እና 109 ሺህ 222 ኩንታል ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ ማዋል መቻሉን አቶ ተውልኝ አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅትም የለማውን ሰብል በማረም፣ተባይን በመከላከልና በመንከባከብ ተግባር ላይ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በዞኑ የሞረትና ጅሩ ወረዳ የገርባ ቀበሌ አርሶ አደር መዝገቡ ወልዴ በበኩላቸው፣ ሰባት ነጥብ አምስት ሄክታር መሬታቸውን በኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴ በመጠቀም በስንዴና አተር ሰብል መሸፈናቸውን ተናግረዋል።   ምርታማነትን ለማሳደግ ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘርና ሌሎች ቴክኖሎጅዎችን ከመጠቀም ባሻገር፣ የአረምና የተባይ መከላከል ስራ እያካሄዱ መሆኑንም ገልጸዋል። በዞኑ የመርሐቤቴ ወረዳ ሰባጌ ሀሮ ገንዳ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት ቄስ አውግቸው ማሞ በበኩላቸው፣ መሬታቸውን በኩታ ገጠም አሰራር ተጠቅመው በጤፍ፣ ማሽላና ባቄላ ሰብል መሸፈናቸውን አስታውቀዋል። ከዞኑ ግብርና መምሪያ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በዞኑ ከ2018/19 የመኸር ምርት ዘመን 20 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማምረት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል።    
በአፋር ክልል ገቢን በተቀናጀ መንገድ የመሰብሰብ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል
Aug 15, 2026 290
ሰመራ፤ ነሐሴ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል ገቢን በተቀናጀ መንገድ የመሰብሰብ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የመሬት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡመር ኑር ተናገሩ። በክልሉ ያለፈው በጀት ዓመት አፈፃፀምና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የወረዳ እና የከተማ አስተዳደር የሥራ ኀላፊዎች በተገኙበት ውይይት ተካሂዷል።     የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የመሬት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡመር ኑር እንዳሉት የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የክልሉን ገቢ በቅንጅት የመሰብሰቡ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል። የበጀት ዓመቱን የገቢ ዕቅድ ለማሳካት በሚከናወኑ ቅንጅታዊ ሥራዎች በየደረጃ የሚገኘው አመራር ወሳኝ ሚና እንዳለውም ጠቁመዋል። ለመሰብሰብ የተያዘውን የገቢ ዕቅድ ለማሳካት የግብር ስወራን በቅንጅት ከመቆጣጠር ባለፈ ህብረተሰቡ ግብሩን በተለያዩ አማራጮች እንዲከፍል ግንዛቤውን የማሳደግ ሥራ እንደሚሰራም አመልክተዋል። ከዚህ በተጨማሪ የገቢ ዕቅዱን ለማሳካት ባለፈው ዓመት በቅንጅት በተከናወኑ ሥራዎች የተገኘውን ወጤት በመቀመር ይሰራል ሲሉም አክለዋል። የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ አወል አብዱ በበኩላቸው እንዳሉት በክልሉ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ ለመሰብሰብ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል። ከዓመት ወደ ዓመት ገቢን የመሰብሰብ አቅም እያደገ መምጣቱን ገልፀው የዘንድሮውን ዓመት በተያዘለት የጊዜ ገደብ ሰብስቦ ለማጠናቀቅ በትጋት ይሰራል ብለዋል። አመራሩ ለገቢ ዕቅዱ መሳካት በተናበበ መልኩ ከመስራት ባለፈ ለሚያጋጥሙ ችግሮች በጋራ መፍትሄ እየሰጠ መሄድ እንዳለበትም አስገንዝበዋል። በተለይም ከዚህ ቀደም የሚስተዋሉ ደረሰኝ አለመቁረጥና ሌሎች መሰል ችግሮችን ለማስወገድ ለንግዱ ማህበረሰብ ግንዛቤ እየሰተጠ መሆኑንም አመልክተዋል። ክልሉ በዘንድሮ በጀት ዓመት ከ16 ቢሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ አቅዶ ወደ ሥራ መገባቱ የሚታወስ ነው።    
ህዝቡ የጸረ ሙስና ትግሉ ባለቤት እየሆነ መጥቷል
Aug 15, 2026 134
አዳማ፤ ነሐሴ 09/2018 (ኢዜአ)፦ በሀገሪቱ ግንዛቤ ለመፍጠር በተሰሩ ስራዎች ህዝቡ የጸረ ሙስና ትግሉ ባለቤት እየሆነ መምጣቱን የፌዴራል ሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሙኤል ኡርቃቶ (ዶ/ር) አስታወቁ። ኮሚሽኑ ያሰናዳው በ17ኛው ሀገር አቀፍ የሥነምግባርና የፀረ- ሙስና ኮሚሽኖች ትስስር ጉባኤ ዛሬ በአዳማ ተካሂዷል። የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ሳሙኤል ኡርቃቶ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በፀረ ሙስና እና ስነ ምግባር ረገድ በተከናወኑ ተግባራት ዋነኛውና ትልቁ ማእቀፍ የሆነው የትውልድ ሥርዓት ግንባታ ጥሩ አቅጣጫ ይዟል። በዚህ ረገድ በፀረ ሙስና ትግል ዙሪያ በየደረጃው ለሚገኘው ሕዝብ ግንዛቤን ለማስረፅ በተሰራው ስራ ህዝቡ የሙስና ትግሉ ባለቤት እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል። ህዝቡ ሙስና በሀገሪቱ የመልካም አስተዳደር፣ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊ እና የሰላም አለመረጋጋትን ከሚፈጥሩ ችግሮች መካከል አንዱ እና ዋነኛው ተግዳሮት መሆኑን በጽኑ አቋም በማመን መንግሥት ችግሩን እንዲገታ ያላውን አቋም በተለያዩ መድረኮች ማሳወቁ ለፀረ ሙስና ትግሉ ትልቅ አቅም ነው ብለዋል። አሁን ላይ መንግሥት በሙስና ላይ የያዘው አቋምና እርምጃ ችግሩን ለማስወገድ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ በተለይም ትግሉን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ጊዜው የሚጠይቀውን የአሰራር፣ የትብብርና የቅንጅት ስራን ተግባራዊ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን አመላክተዋል። ኮሚሽኑ ባለፈው በጀት ዓመት የፀረ ሙስና ትግሉ በሥነ ምግባር ግንባታ፣ ሙስናን አስቀድሞ መከላከልና ሕግ ማስከበር እንዲሁም የአንድ ዕቅድ የአንድ ሪፖርት ስትራቴጂዎች በመካከለኛ ዘመን ዕቅድ ጋር በማስተሳሰር ውጤታማ አፈጻጸም ማከናወኑን አብራርተዋል። የክልልና የከተማ አስተዳደር የሥነ ምግባርና የፀረሙስና ኮሚሽኖች ቀደም ሲል 16 ዙር ሀገር አቀፍ የትስስር ጉባኤዎች መካሄዳቸው ለጸረ ሙስና ትግሉ ፍሬያማ እንዲሆን ምቹ መደላድል መፍጠሩንም አንስተዋል። በ17ኛው ጉባዔም በ2018 በጀት ዓመት ሲከናወኑ በነበሩ የሥነ ምግባር ግንባታና ሙስና መከላከል ስራዎች በጥልቀት በመወያየት ጠንካራና ደካማ ጎኖችን በመለየት በቀጣይ የተሻለ ስራ ለመስራት የሚያስችል አቅጣጫ መቀመጡን ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል። በጉባዔው ላይ የ2018 በጀት ዓመት የሥራ ሪፖርት ያቀረቡት በኮሚሽኑ የዲጂታል ሙስና መረጃ አስተዳደር መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን በላይነህ፤ የ2018 በጀት ዓመት የፀረ-ሙስና ትግል በዘርፍ-ተኮር፣ ችግር ፈቺ እና ተቋማዊ አሰራር ላይ በማተኮር መከናወኑን አስታውቀዋል። በዓመቱ የሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና መከላከል ሥራዎች ለማስፈጸም የአቅም ግንባታና ሥልጠናዎች፣ የሙስና መከላከል ጥናቶች፣ የአስቸኳይ ሙስና መከላከል ተግባራት፣ የሀብት ማሳወቅና ምዝገባ ሥራዎች በፌዴራል ተቋማትና በሕዝባዊ ድርጅቶች በተጠናከረ ሁኔታ መፈጸማቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል። ኮሚሽኑ ከሕግ አስከባሪ ተቋማት ጋር ትስስሩን በማጠናከር ከተለያዩ ምንጮች የሙስና ወንጀል መረጃ በመሰብሰብና በመተንተን ለሚመለከታቸው አካላት ማቅረቡንም አውሰተዋል። በመድረኩ ላይ ከአዲስ አበባና ድሬዳዋ አስተዳደርን ጨምሮ ከሁሉም ክልሎች የተውጣጡ ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በምስራቅ ሐረርጌ  ዞን ቁንቢ ወረዳ  የተገነቡ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች ተመርቀው አገልግሎት መስጠት ጀመሩ
Aug 15, 2026 169
ቁንቢ፤ ነሐሴ 09/2018 (ኢዜአ) ፦ በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ቁንቢ ወረዳ በ640 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች ተመርቀው አገልግሎት መስጠት ጀመሩ። በወረዳው ሀሮ ጉራቲ እና ሀሪሮ ቀበሌዎች የተገነቡትን ፕሮጀክቶች መርቀው ሥራ ያስጀመሩት የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሡልጣን ወሊ (ዶ/ር) እና ሌሎች የክልሉና የምስራቅ ሐረርጌ ዞን አመራር አባላት ናቸው። በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በኢነርጂ ዘርፍ ከሚተገበሩ የልማት ተግባራት መካከል የብሔራዊ ኤሌክትሪፊኬሽን ፕሮግራም ሲሆን የኢትዮጵያ ኤልክትሪክና ብርሃን ተደራሽነት ፕሮጀክት ደግሞ በዚህ ፕሮግራም ስር ይከናወናል። ከዋናው የብሔራዊ የኤሌክትሪክ መስመር ርቀው በሚገኙ እንደ ቁምቢ ወረዳ ሃሮ ጉራቲ እና ሃሪሮ ባሉ የገጠር ቀበሌዎች የሚዘረጉ የሶላር ሚኒ ግሪዶች ፣ ዘላቂና ንጹህ የሃይል አማራጭን ለህብረተሰቡ ለማቅረብ የተነደፉ ናቸው። የምስራቅ ሐረርጌ ዞን፣ በተለይም ቁምቢ ወረዳ እና አካባቢው በቆላማና በከፊል አርብቶ አደር አየር ንብረት ክልል ውስጥ የሚገኙ በመሆናቸው በንጹህ መጠጥ ውሃ እጥረትና ተደጋጋሚ የድርቅ ስጋት የሚታይባቸው አካባቢዎች ናቸው። አሁን በእነዚህ ቀበሌዎች የተገነቡትን የውሃ እና የኢነርጂ ፕሮጀክቶች አጠናቆ ማስመረቅ ለአካባቢው ማህበረሰብ ዘላቂ ጥቅም የሚያስገኝ ትልቅ እርምጃ መሆኑ ነው የተገለጸው። 640 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገባቸው ፕሮጀክቶቹ 850 ኪሎ ዋት ኃይል የማመንጨት አቅም እንዳላቸውና የ24 ሰዓት አገልግሎት መስጠት እንደሚችሉ በምረቃው ሥነ ሥርዓት ላይ ተገልጿል። ፕሮጀክቶቹ 3ሺህ 646 አባወራዎችን እንዲሁም የጤና፣ ትምህርትና ሌሎች ማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማትን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ተጠቁሟል። የወረዳው ነዋሪዎች በፕሮጀክቱ ግንባታ የዘመናት የልማት ጥያቄያቸው በመመለሱ ደስተኛ መሆናቸውን ነው የገለጹት። በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የፌዴራልና የክልል፣ የዞንና ወረዳ አመራር አባላት፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የእንስሳት ህገ-ወጥ ንግድን ለመከላከል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው
Aug 15, 2026 621
ጂንካ፤ነሐሴ 9/2018(ኢዜአ):- የእንስሳት ሃብት ህገ-ወጥ ንግድን ለመከላከልና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ ደቡብ ኦሞ ዞን የቀይ አፈር-የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል ግንባታ በመገባደድ ላይ ሲሆን በቅርቡ ተጠናቆ ለአገልግሎት ይበቃል ተብሏል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊና ንግድና ገበያ ልማት ዘርፍ ኃላፊ ወይዘሮ ፍቅርተ አብርሃም፤ በክልሉ ያለው ሰፊ የእንስሳት ሃብት ልማት ለዜጎች የተሻለ ጥቅም እንዲሰጥ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። በእንስሳት ሃብት ላይ የሚስተዋለውን ህገ-ወጥ ንግድ ለመከላከልና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛልም ብለዋል። የቁም እንስሳትን ወደ ግብይት ማዕከላት በማቅረብ በተሻለ ዋጋ ለማህበራትና ለዩኒየኖች ለማቅረብ የሚያስችል አሰራር ስለመዘርጋቱ አንስተዋል። በኤክስፖርት እንስሳት ማሰባሰቢያ ማዕከላት አማካኝነት በሀገሪቱ ለሚገኙ የኤክስፖርት ቄራዎች ዩኒየኖች በቀጥታ የሚያቀርቡበት ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል።   በክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ የአርብቶ አደር አደጋ ስጋት ቅነሳና አካታች የኢኮኖሚ እሴት ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ ስዩም መታፈሪያ (ዶ/ር)፤ የእንስሳት ሀብት በብዛት በሚገኝባቸው የክልሉ አካባቢዎች የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከላት እየተገነቡ መሆኑን ጠቅሰዋል። የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከላት የኤክስፖርት ስታንዳርዱን የጠበቁ እንስሳትን ማቅረብ በሚያስችል መልኩ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም የኤክስፖርት ቄራዎችን እና የተቀባይ አገራትን ፍላጎት ያማከለ የቁም እንስሳት በብዛትና በጥራት በማቅረብ ሀገሪቱ ከፍተኛ የውጪ ምንዛሪ እንድታገኝ በቅንጅት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።   የቱርሚ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሀማ አይኬ፤ በከተማ አስተዳደሩ የተገነባው የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል በተለይም አርብቶ አደሩን ተጠቃሚ በማድረግ ረገድ ትልቅ ትርጉም ይኖረዋል ሲሉ ተናግረዋል። የቁም እንስሳት ንግድ ህጋዊ ስርአቱን የተከተለ ሲሆን የመንግስት የገቢ ምንጭ እንደሚሆንና በከተማው ለሚገነቡ መሰረተ ልማቶች መሳለጥም ወሳኝ እንደሆነ ገልጸዋል። በቅርቡ ግንባታው ተጠናቆ የተመረቀው የኤክስፖርት እንስሳት ማሰባሰቢያ ማዕከል ኢትዮጵያ ከእንስሳት ሀብቷ ተገቢውን ጥቅም የምታገኝበትን ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑ ታውቋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት በታሪክ መነፅር ሲቃኝ ግልጽና የማያሻማ ነው
Aug 15, 2026 293
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 9/2018 (ኢዜአ) ፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት በታሪክ መነፅር ሲቃኝ ግልጽና የማያሻማ ነው ሲሉ ምሁራን ገለጹ። ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሀብቶቿንና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋን ለታዳሽ ኃይል ልማት፣ ቀጣናዊ ትብብር፣ ለጋራ እድገትና ልማት በማዋል ግንባር ቀደም ሚና አላት፡፡ ቅድሚያ ለጎረቤት ሀገራት የሚለው የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ የቀጣናውን ሀገራት በመሰረተ ልማት በማስተሳሰር የጋራ ሰላምና ብልጽግና ማረጋገጥ የሚያስችልም ነው፡፡ የታሪክ ተመራማሪው ፕሮፌሰር አህመድ ዘካሪያ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት የኢትዮጵያ የቀይ ባህር ባለቤትነት በታሪክ መነፅር ሲቃኝ ግልጽና የማያሻማ ነው። የሀብት ስርጭትንና የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀምን በተመለከተም ኢትዮጵያ ከአፍሪካውያን ጋር በጋራ በመጠቀም አህጉራዊ ትብብርን የማጠናከር ፍላጎት አላት ብለዋል። አፍሪካውያን የተፈጥሮ ሀብቶቻቸውን በጋራና በወንድማማችነት ስሜት መጠቀም አለባቸው ያሉት ፕሮፌሰር አህመድ፤ ኢትዮጵያ ቀጣናውን በውሃና ሀይል ማስተሳሰሯንም ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ የቀጣናው ልማትና ደህንነት መልህቅ መሆኗን በመግለጽ፤ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ስራዎችን በመስራትም ግንባር ቀደም መሆኗን ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከባህር በር የተገለለችው የቀድሞው ህወሓትና ሻዕቢያ የግል ጥቅማቸውን ለማስከበር ሲሉ በፈጠሩት አግላይ አካሄድ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ጥቅሟን የሚያስከብሩ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች እያደረገች መሆኑን ገልጸው፤ ቀጣናዊ የዲፕሎማሲ መድረኮችም ጨምረዋል ብለዋል፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ የባህር በር ያስፈልጋታል የሚለው መሠረታዊ እውነትና ፍላጎት በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ አወንታዊ ምላሽ እያገኘ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የቀጣናው ሀገራት በመተጋገዝና በመተባበር አቅማቸውን ማጎልበትና የጋራ ልማትና ዕድገትን ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል፡፡ በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር የዲጂታል ዲፕሎማሲ ዳይሬክተር ስለአባት ማናየ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ቀጣናዊና አህጉራዊ ትብብርን ማጠናከር መርሁ ያደረገ ነው፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት መሥራችና መቀመጫ፣ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት መገኛ እና ለባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ ትኩረት የምትሰጥ ሀገር መሆኗንም ገልጸዋል። ዓባይን ጨምሮ ወንዞቿን የቀጣናዊ ትስስር፣ የጋራ ዕድገትና የትብብር ማሳያ አድርጋ እንደምትመለከት ገልጸው፤ በዚህም የቀጣናው የታዳሽ ኃይልና የጋራ የልማት መሪነቷን አስጠብቃለች ብለዋል፡፡ የአፍሪካ ሕብረት "አጀንዳ 2063" ለቀጣናዊ የኢኮኖሚያዊ ውህደት ትኩረት እንደሚሰጥ በማንሳት፤ ኢትዮጵያ የሕብረቱን ራዕይ በፅናት ተቀብላ ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዓባይ ፖለቲከኞች ሴራና በራሳችን ድክመት ለዘመናት ስትጠቀምበት የቆየችውን ቀይ ባህር ማጣቷን አንስተዋል አቶ ስለአባት፡፡ ይሄንን ታሪካዊ ስህተት በማረም ህጋዊ መብቷን ለማስከበር ቀይ ባህርን ወደ ቤቱ የመመለስ እንቅስቃሴ ተጀምሯል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ የህልውና ጉዳይ የሆነው የቀይ ባህር ጥያቄ ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ አንድምታው ከፍተኛ መሆኑን በማንሳት፤ በቀጣናው ያላትን ስትራቴጂያዊ አቅም የሚበይን መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ በዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ዘንድ ጆሮ ገብ እየሆነ መምጣቱን ገልጸው፤ ለቀጣናው ኢኮኖሚያዊ ትብብርና ሰላም የጎላ አበርክቶ ይኖረዋል ብለዋል፡፡
ወጣቶችን በክህሎትና በአመለካከት ብቁ በማድረግ በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ለውጥ ማምጣት ተችሏል
Aug 14, 2026 777
ሐዋሳ፤ ‎ነሐሴ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል ወጣቶችን በክህሎትና በአመለካከት ብቁ በማድረግ በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትርጉም ያለው ለውጥ ማምጣት መቻሉን የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ፡፡ በኢትዮጵያ ኢንተርፕርነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት ለወጣቶች ቀጣይነት ያለው የሥራ ዕድል ፈጠራ ፕሮግራም ''SEED'' በሲዳማ ክልል የሦስት ዓመት የሥራ አፈጻጸምና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ የሚመክር መድረክ በሐዋሳ ከተማ ተካሄዷል፡፡   የሲዳማ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሀገረጽዮን አበበ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ በክልሉ ወጣቶችን በክህሎትና በአመለካከት በማብቃት በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትርጉም ያለው ለውጥ ማምጣት ተችሏል፡፡ ከዚህ ቀደም የነበረው የሥራ ዕድል ፈጠራ ክህሎት መር ባለመሆኑ የተነሳ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ዜጎች ውጤታማ አለመሆን የዘርፉ ፈተና ሆኖ መቆየቱን አስታውሰዋል። ዘርፉ በዜጎች ክህሎትና አመለካከት ላይ የተመሠረተ እንዲሆን እንደ ሀገር አቅጣጫ ተይዞ መሥራት ከተጀመረ በኋላ፤ በተለይ ወጣቶች በተሻለ አቅምና ፍላጎት ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን ጠቁመዋል፡፡   በዚህም ውጤታማ የሆኑና ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች የሥራ ዕድል መፍጠር የቻሉ በርካታ ወጣቶችን ማፍራት እንደተቻለ ጠቅሰው፤ በዚህ ረገድ የባለድርሻ አካላት ቅንጅት ከፍተኛ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የቢሮው ምክትልና የሥራ ዕድል ፈጠራ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ከፍያለው ከበደ በበኩላቸው፤ አጋር አካላትን ከሥልጠና ተቋማት ጋር በማቀናጀት የክህሎት ክፍተቶችን የመሙላት እና ወደ ሥራ የሚገቡትን የማብቃት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡   ቅድሚያ ለክህሎትና አመለካከት በመስጠት የፋይናንስ፣ እንዲሁም የመሥሪያና የመሸጫ ቦታዎችን የማቅረብ ሥራ እየተሠራ መሆኑንም አክለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ኢንስቲቲዩት የሲዳማ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ፣ የደቡብ ኢትዮጵያና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልሎች አስተባባሪ አቶ ጌትነት ሳሙኤል፤ በኢንስቲትዩቱ የሚመራው የሥራ ዕድል ፈጠራ ፕሮግራም በአምስት ዓመታት ውስጥ ለ1 ሚሊዮን ወጣቶች ቀጣይነት ያለው የሥራ ዕድል የመፍጠር ዕቅድ አለው ብለዋል፡፡   ፕሮግራሙ ከተመረጡ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ጋር በመሆን የክህሎት ሥልጠና የመስጠት፣ እንዲሁም ከፋይናንስ ተቋማት ጋር በመቀናጀት የብድር አቅርቦት የማመቻቸት ሥራ እንደሚሠራ አስረድተዋል፡፡ በፕሮግራሙ በሲዳማ ክልል በሦስት ዓመታት ውስጥ ከ27 ሺህ በላይ ወጣቶች የክህሎት ሥልጠና ያገኙ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ19 ሺህ በላይ የሚሆኑት የሥራ ዕድል እንደተፈጠረላቸው አብራርተዋል፡፡ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር በመቀናጀትም ለኢንተርፕራይዞች ከ181 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር እንደተሰራጨ ጠቁመዋል፡፡   በፕሮግራሙ ድጋፍ ካገኙ ኢንተርፕራይዞች መካከል የጠይም ጋርመንት አባል የሆነችው ወጣት ቤርሳቤህ አለማየሁ እና የጃዋታ ጨርቃ ጨርቅ ማኅበር አባል የሆነችው ወጣት ራህመት ሁሴን፤ በፕሮግራሙ ባገኙት ሥልጠና ከዚህ ቀደም የነበረባቸውን የሂሳብ አያያዝና ሌሎች ክፍተቶች በመሙላት በሥራቸው ትርፋማ መሆን እንደቻሉ ገልጸዋል፡፡   በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ተቋማት አመራሮች ተገኝተዋል፡፡  
የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ የሚወስዱበት ነው
Aug 14, 2026 667
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ የሚወስዱበት መሆኑን በኢትዮጵያ እና በአፍሪካ ሕብረት የሳህራዊ ሪፐብሊክ አምባሳደር ላሚን ባአሊ ገለጹ። አምባሳደር ባአሊ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ እና በሌሎች ዘርፎች ስኬታማ ጉዞ እያደረገች እንደምትገኝ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ስኬታማ ጠቅላላ ምርጫ ማካሄዷንም አንስተዋል። ይህ ከፍተኛ የሕዝብ ተሳትፎ ዜጎች የፖለቲካ ኃላፊነታቸውን ለመወጣት ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ አዎንታዊ ማረጋገጫ እንደሆነም ነው የተናገሩት። በምርጫው የፖለቲካ ፓርቲዎች በንቃት መሳተፋቸውን በመጥቀስ፣ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ግንባታ ሂደት ውስጥ በጎ እርምጃ መሆኑንም አምባሳደር ባአሊ አስረድተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሚመራው የሪፎርም አጀንዳ በሀገሪቱ ውስጥ ለበለጠ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ልማት ዕድገት አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። ከኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ጋር በተጣጣመ መልኩ የሚከናወኑ የተለያዩ የልማትና የለውጥ ሥራዎች አዎንታዊ ውጤት እያመጡ እንደሚገኙም ጠቁመዋል። በሀገሪቱ እየተተገበረ ያለው የኢኮኖሚ ሪፎርም የዜጎችን ኑሮ ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑን ጨምረው አንስተዋል፡፡ ይህ በኢትዮጵያ እውን እየሆነ ያለው ውጤታማ ሪፎርም በዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ዘንድ ከፍተኛ ትኩረትና እውቅና ማግኘቱን ተናግረዋል። በመሆኑም ይህ የኢትዮጵያ ስኬታማ ተሞክሮ በአጠቃላይ በአፍሪካ ደረጃ የሚገኙ ሌሎች ሀገራት ትምህርት ሊወስዱበት የሚችል ነው ብለዋል። ሀገራዊ ምክክር አስፈላጊ የፖለቲካ ልምምድ እንደሆነ የጠቆሙት አምባሳደሩ፣ በኢትዮጵያ እየተደረገ የሚገኘው ሀገራዊ ምክክር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። የሀገራዊ ምክክር ሂደቱ ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠርና ለሁሉም አካላት ዘላቂ ጥቅም ለማስገኘት ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ ተናግረዋል። በሳህራዊ ሪፐብሊክ እና በኢትዮጵያ መካከል እ.ኤ.አ ከ1970ዎቹ ጀምሮ የነበረውን ትብብር አውስተው፣ የሀገራቱ ግንኙነት ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቅሰዋል። ባህል፣ ስፖርት፣ ንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ጤና እና ሌሎች የጋራ ፍላጎት በሆኑ ዘርፎች የሁለትዮሽ ትብብሩን የበለጠ ለማስፋት እንደሚሰራም አምባሳደር ላሚን ባአሊ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም