ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በክልሉ በቱሪዝም ዘርፍ 978 ሚሊዮን ብር ገቢ ተገኝቷል
Sep 7, 2026 265
ጂንካ፥ ጳጉሜ 2/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት አመት በቱሪዝም ዘርፍ 978 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን የክልሉ ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ወይኒቱ መልኩ በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት አመት ከቱሪዝም ዘርፍ 500 ሚሊዮን ብር ገቢ ለማግኘት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን አስታውሰዋል። ይሁን እንጂ ለዘርፉ በተሰጠው ትኩረት ከእቅድ በላይ 978 ሚሊዮን ብር መገኘቱን ተናግረዋል። በክልሉ የቱሪዝም መዳረሻዎችን የማልማትና የማስተዋወቅ ስራ በስፋት በመሰራቱና የጎብኚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ለገቢው ማደግ በምክንያትነት ጠቅሰዋል።   የሙሩሌ የቁጥጥር አደን ቦታ፣ የማጎና የማዜ ብሔራዊ ፓርኮች የኮንሶ ባህላዊ መልክዓ ምድር ዓለም አቀፍ መካነ ቅርስ በክልሉ ከሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎች ዋነኞቹ እንደሆኑ ጠቁመዋል። የአርባምንጭ አዞ እርባታ፣ የባንባላ ተንጠልጣይ ድልድይ፣ የዳሞ ተራራና የጌዴኦ ትክል ድንጋዮች መካነ ቅርስም በስፋት እየተጎበኙ ያሉ የመስህብ ስፍራዎች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በበጀት አመቱ 13 ሚሊዮን የሀገር ውስጥና የውጪ ቱሪስቶች የመስህብ ስፍራዎቹን መጎብኘታቸውን ተናግረዋል።   በክልሉ የጎብኚዎች ቁጥር መጨመርም ለቢዝነስ ቱሪዝም መነቃቃት እና ለስራ እድል ፈጠራ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስታውቀዋል። የማጎ ብሔራዊ ፓርክ አስተዳዳሪ አቶ ኤርቦር ሌለ በበኩላቸው ፓርኩን ለመመልከት ወደ ስፍራው የሚመጡ ጎብኚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ተናግረዋል። ፓርኩ ከ80 በላይ አጥቢ፣ ከ250 በላይ የአዕዋፍና 14 ዓይነት የዓሣ ዝርያዎችን የያዘ መሆኑን አመልክተዋል።  
በአዲስ አበባ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የሀገሪቱን የማንሰራራት ጉዞ የሚያፋጥኑ ናቸው
Sep 7, 2026 259
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ) ፦ በአዲስ አበባ የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎችና ሌሎች የመሠረተ ልማት ሥራዎች የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ የሚያፋጥኑ መሆናቸውን ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጳጉሜን 02 "የማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በአዲስ አበባ የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎችንና የመሠረተ ልማት ሥራዎችን ለተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች አስጎብኝቷል።   በጉብኝት መርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉ ጎብኚዎች በአዲስ አበባ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ከተማዋ ለአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ እንድትሆን ያስቻሉ ናቸው ብለዋል፡፡ አስተያየት ሰጪ ሻምበል ዋኘው አባይ እንዳሉትም ከተማዋ ከዚህ ቀደም ከነበራት ገጽታ በተለየ መልኩ ውብና ጽዱ መሆኗን ገልጸው፤ የወንዝ ዳርቻ፣ የኮሪደር ልማትና የቱሪዝም መዳረሻዎች የሀገሪቱን ዕድገት የሚያንሰራሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። አቶ ገዛኸኝ አሰፋ በበኩላቸው የመሠረተ ልማት ሥራዎቹ ለዜጎች የሥራ ዕድል የፈጠሩ፣ ለነዋሪዎችና ለጎብኚዎች ምቹ አካባቢን የፈጠሩ መሆናቸውን በአካል ማረጋገጣቸውን ገልጸዋል፡፡ እነኚህም የኢትዮጵያን የማንሰራራት ግስጋሴ የሚያፋጥኑ ናቸው ብለዋል፡፡ የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን በመገናኛ ብዙኃን ከማየት ባለፈ በአካል መጥተው በመጎብኘታቸው መደሰታቸውን የገለጹት ሐጂ ሸምሱ አባስ ፤ የከተማዋ ዕድገት ለሀገር ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሙኒኬሽን ኃላፊ ልደት ሙለታ ጳጉሜን 02 "የማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በለውጡ ዓመታት ለነዋሪዎች ውብና ጽዱ ከተማን ለመፍጠርና በቱሪዝም ዘርፍ የተከናወኑ ሥራዎችን ማስጎብኘታቸውን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎች፣ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ተግባራት የሀገሪቱን ዕድገት ያረጋገጡ መሆናቸውንም ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጳጉሜን 02 "የማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በአዲስ አበባ የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎችንና የመሠረተ ልማት ሥራዎችን ለተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች አስጎብኝቷል። በጉብኝት መርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉ ጎብኚዎች በአዲስ አበባ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ከተማዋ ለአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ እንድትሆን ያስቻሉ ናቸው ብለዋል፡፡   አስተያየት ሰጪ ሻምበል ዋኘው አባይ እንዳሉትም ከተማዋ ከዚህ ቀደም ከነበራት ገጽታ በተለየ መልኩ ውብና ጽዱ መሆኗን ገልጸው፤ የወንዝ ዳርቻ፣ የኮሪደር ልማትና የቱሪዝም መዳረሻዎች የሀገሪቱን ዕድገት የሚያንሰራሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። አቶ ገዛኸኝ አሰፋ በበኩላቸው የመሠረተ ልማት ሥራዎቹ ለዜጎች የሥራ ዕድል የፈጠሩ፣ ለነዋሪዎችና ለጎብኚዎች ምቹ አካባቢን የፈጠሩ መሆናቸውን በአካል ማረጋገጣቸውን ገልጸዋል፡፡ እነኚህም የኢትዮጵያን የማንሰራራት ግስጋሴ የሚያፋጥኑ ናቸው ብለዋል፡፡ የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን በመገናኛ ብዙኃን ከማየት ባለፈ በአካል መጥተው በመጎብኘታቸው መደሰታቸውን የገለጹት ሐጂ ሸምሱ አባስ ፤ የከተማዋ ዕድገት ለሀገር ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሙኒኬሽን ኃላፊ ልደት ሙለታ ጳጉሜን 02 "የማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በለውጡ ዓመታት ለነዋሪዎች ውብና ጽዱ ከተማን ለመፍጠርና በቱሪዝም ዘርፍ የተከናወኑ ሥራዎችን ማስጎብኘታቸውን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎች፣ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ተግባራት የሀገሪቱን ዕድገት ያረጋገጡ መሆናቸውንም ተናግረዋል።
በደቡብ ወሎ ዞን በተለያዩ ዘርፎች የተመዘገቡ ውጤቶች የኢትዮጵያ የማንሰራራት ተምሳሌት ናቸው
Sep 7, 2026 264
ቃሉ፤ ጳጉሜን 2/2018(ኢዜአ)፡-በደቡብ ወሎ ዞን በኢንቨሰትመንት፣ በቱሪዝም፣ በግብርና፣ በፍራፍሬ እና የኮሪደር ልማት መስኮች የተመዘገቡ አበረታች ውጤቶች የኢትዮጵያ ማንሰራራት በተጨባጭ የሚያረጋግጡ መሆናቸውን የዞኑ መስተዳድር ገለፀ። በዞኑ የማንሰራራት ቀን ምክንያት በማድረግ በቃሉ ወረዳ እና ሀርቡ ከተማ የተለያዩ የልማት ሥራዎች ጉብኝት ተካሂዷል። በጉብኝቱ የደቡብ ወሎ ዞን አስተዳደር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ እንድሪስ ይማም እንደገለጹ፣ በዞኑ በተለያዩ የልማት ሥራዎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ በማድረግ አበረታች ውጤት ተመዝግቧል። በተለይ በኢንቨሰትመንት፣ በቱሪዝም፣ በግብርና፣ የፍራፍሬ እና ኮሪደር ልማትን ጨምሮ በከተማ ልማት፣ በንጹህ መጠጥ ውሃና በሌሎችም የተመዘገቡ ተስፋ ሰጪ ውጤቶች የኢትዮጵያ እያንሰራራች መሆኑን ያመላክታሉ ነው ያሉት። በከተሞቹ የጠጠር ማምረቻ፣ የኮሪደር ልማት፣ ተንጠልጣይ ድልድይና ሌሎችም ልማቶች ተስፋ ሰጪ እና የኢትዮጵያን ማንሰራራት ለማስቀጠል የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልፀዋል። የዞኑ ማዕድን ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ አበባው በበኩላቸው፣ በዞኑ ከሚገኘው በርካታ የማዕድን ሀብት በአግባቡ እና በዘላቂነት ተጠቃሚ ለመሆን እየተሰራ ነው ብለዋል። የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በከተማው በተሰሩ ሰፋፊ ልማቶች ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የሀርቡ ከተማ ነዋሪ ሸህ ሰይድ ሀሰን እና ሹምነሽ ኢብራሂም ናቸው። በተለይ የኮሪደር ልማቱ የከተማውን ውበት በማሳመር ለነዋሪዎች ምቹ የሥራ አከባቢን የፈጠረ ሲሆን በወረዳው እየተገነቡ ባሉ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶች ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልፀዋል። ከዚህ ውስጥም በተገነቡ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ችግራቸው በመቀረፉ መደሰታቸውን ገልጸዋል። በጉብኝቱ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አመራሮችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።  
የመደመር መንግስት በተለያዩ ዘርፎች ያከናወናቸው ተግባራት የኢትዮጵያን ማንሰራራት ለማረጋገጥ ያስቻሉ ናቸው
Sep 7, 2026 263
ደብረማርቆስ፤ ጳጉሜ 2/2018(ኢዜአ)፡- የመደመር መንግስት በተለያዩ ዘርፎች ያከናወናቸው ተግባራት የኢትዮጵያን ማንሰራራት በተግባር ለማረጋገጥ ያስቻሉ ናቸው ሲል የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ። ከተማ አስተዳደሩ የማንሰራራት ቀንን አስመልክቶ ከተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ጋር የፓናል ውይይት አካሒዷል።   የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ የኋላ ደስታ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ የመደመር መንግስት ተግባራዊ ባደረጋቸው የኢንዱስትሪ፣ የከተማ ግብርናና የሰው ተኮር ፕሮጀክቶች ከፍተኛ ስኬቶች ተመዝግበዋል። ከዚህ ውስጥም በከተማ አስተዳደሩ ከ10 ዓመት በፊት ከአስር በታች የነበረው የአምራች ኢንዳስትሪዎች ቁጥር አሁን ላይ ከ70 በላይ ማድረስ የተቻለ ሲሆን 39 የሚሆኑት ወደ ማምረት የተሸጋገሩ መሆኑን አረጋግጠዋል። በማህበራዊ ዘርፍም በቅድመ አንደኛ ደረጃ፣ በ1ኛና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተደራሽነት፣ ጥራትና አግባብነት ውጤታማ የሆኑ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። ከ500 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪም ሞዴል ትምህርት ቤት ግንባታ በመጠናቀቅ ላይ መገኘቱ የማንሰራራት ማሳያ እንደሆነም አብራርተዋል። በስራ እድል ፈጠራ፣ በከተማ ግብርና፣ በመሰረተ ልማት ግንባታና በሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን አስገንዝበዋል። ከተሳታፊዎች መካከል ሊቀ ካህናት ይትባረክ መኮነን እና ወንዳለ ተመስገን እንዳሉት ፤ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኮሪደርና ሌሎች ልማቶች የታየው ለውጥ ይበል የሚያሰኝ በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተናግረዋል። በተለይ በከተማ ግብርና ፣ በኢንድስትሪ እና መሰል ስሰራዎች ላይ ያከናወናቸውን ተግባራት ውጤት መምጣቱን ተዘዋውረው መመልከታቸውን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ሀገራዊ ማንሰራራትን የሚያፀኑ ሜጋ የልማት ፕሮጀክቶች አከናውናለች
Sep 7, 2026 266
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ሀገራዊ ማንሰራራትን የሚያፀኑ ሜጋ የልማት ፕሮጀክቶች ማከናወኗን የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለሥልጣን ገለጸ። ዛሬ የጳጉሜን 2 የ"ማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ የስድስት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችን ዐበይት የልማት እንቅስቃሴዎች የሚያሳይ የፎቶ አውደ ርዕይ ሲከፈት የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍራኦል ጣፋ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያን ማንሰራራት የሚያፀኑ የልማት ሥራዎች በፍጥነት እየተከናወኑ ነው። መንግስት በሁሉም ተቋማት የሕዝቡን ጥያቄዎች በመመለስ የኢትዮጵያን ተስፋ የሚያለመልሙ ትልልቅ ሜጋ ፕሮጀክቶችና ኢኒሼቲቮች ቀርፆ ወደ ስራ መግባቱን ገልጸዋል።   የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አገልግሎቱን የሚያዘምኑ በርካታ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች መከናወናቸውን ገልጸው፤ የፎቶ አውደ ርዕዩ ተቋማት በትብብርና በቅንጅት የፈጠሯቸውን ሀገራዊ የልማት ውጤቶችና አቅሞችን በግልጽ ያሳያል ብለዋል። በትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር የኮሙኒኬሽን ስራ አስፈፃሚ አመለወርቅ ህዝቅኤል፤ በትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ የነዳጅ ወጪና የአየር ንብረት ለውጥን ታሳቢ ያደረገ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ግዢ እንደሚፈጸም ገልጸዋል።   የሞጆ ደረቅ ወደብ የአረንጓዴ ሎጂስቲክስ ማስፋፊያ ፕሮጀክት ግንባታ ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ለአገልግሎት ሲበቃ ሀገራዊ የሎጅስቲክስ ምህዳሩን ያዘምነዋል ብለዋል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ሥራ አስፈፃሚ ኢትዮጵያ በዴቻ፤ መንግሥት አዲስ አበባን ጨምሮ በርካታ ከተሞች ገቢራዊ ያደረገው የኮሪደር ልማት የነዋሪዎችን የአኗኗር ዘይቤ መቀየሩን ገልጸዋል።   ከዚህም ባለፈ የመንግሥትና የግሉን አጋርነት በማጠናከር እስከ 10 ዓመታት ይወስዱ የነበሩ የቤት ግንባታዎችን በወራት ውስጥ በማጠናቀቅ ለከተሞች ዝማኔ ገንቢ ሚና ተወጥቷል ብለዋል። በቱሪዝም ሚኒስቴር የኢትዮጵያ ኮንቬንሽን ቢሮ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ብዙዓለም ጌቱ በበኩላቸው፤ መንግሥት ለቱሪዝም ልማት ፖሊሲ በመቅረጽ ዘርፉ የሚያመነጨውን ኢኮኖሚ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል።   እንደ ጅማ አባ ጅፋርና የጎንደር ፋሲለደስ ያሉ ታሪካዊ ቅርሶች ከመጠገን ባለፈ በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገርና ገበታ ለትውልድ የተገነቡ የቱሪዝም ሀብቶች ሀገሪቱን የቱሪስት መዳረሻ አድርጓታል ብለዋል።
ለህዝብ ጥያቄ ፈጣን ምላሽ ለመስጠት ለዲጂታል ሲቪል ሰርቪስ ግንባታ ትኩረት ተሰጥቷል
Sep 7, 2026 63
ደብረ ብርሃን፤ ጳጉሜ 2/2018 (ኢዜአ)፡-የመንግስት ተቋማት ለህዝብ ጥያቄ ፈጣን ምላሽ እንዲሰጡ ለዲጂታል ሲቪል ሰርቪስ ግንባታ ትኩረት መስጠቱን የሰሜን ሸዋ ዞን ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሀብት መምሪያ አስታወቀ፡፡ ጳጉሜ 2 «የማንሰራራት ቀን» አዳዲስ ተስፋዎችን በመሰነቅ፣ ያረጁ አሰራሮችን በዘመናዊ አስተሳሰብ በመተካት ለሀገርና ለህዝብ እድገት በቁርጠኝነት የምንነሳሳበት ልዩ ቀን ነው ሲል መምሪያው አመልክቷል። የመምሪያው ኃላፊ ወይዘሮ ሜሮን አበበ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በዞኑ የማንሰራራት ቀንን ፋይዳ መነሻ በማድረግ አዳዲስ አሰራሮችና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የመንግስት መስሪያ ቤቶች ለህዝብ ጥያቄ ፈጣን ምላሽ እንዲሰጡ እየተደረገ ይገኛል። በተለይም ጠንካራ የሲቪል ሰርቪስ ተቋምን በመገንባት ከብልሹ አሰራር የፀዳ የመንግስት አገልግሎት በመስጠት አገራዊ ማንሰራራቱን በዘላቂነት ለማስቀጠል እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። አክለውም ዘመኑን የሚመጥን የመንግስት አገልግሎት አስተዳደር ሪፎርም በመዘርጋት ነፃና ገለልተኛ የሲቪል ሰርቪስ ተቋም ለመገንባት ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ሙሉ በሙሉ የዲጂታል ሲቪል ሰርቪስ ግንባታን እውን ለማድረግም የመንግስት ሰራተኞችን ትክክለኛ ቁጥር ለማወቅ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል። ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት የአሰራር ባህል እንዲጎለብት በማድረግ ለሙስና የሚያጋልጡ አሰራሮችን ለመቀነስና ዘመናዊ አሰራርን ለመዘርጋት ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑንም አብራርተዋል። ለዚህም በቡልጋ፣ በአረርቲ እና በሸዋ ሮቢት ከተማ አስተዳደሮች የመሶብ አንድ ማዕከል ግንባታ ስራ በፍጥነት እየተከናወነ እንደሚገኝ ወይዘሮ ሜሮን አስረድተዋል። የዲጂታል አሰራር ትግበራው በአገልግሎት አሰጣጥና በመልካም አስተዳደር ለማንሰራራት የሚደረገውን ጉዞ በእጅጉ የሚያፋጥን እንደሆነም አመላክተዋል።  
በሲዳማ ክልል በሁሉም ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶች ሀገራዊ የማንሰራራት ጉዞን የሚያፋጥኑ ናቸው
Sep 7, 2026 44
ሀዋሳ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በሁሉም ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶች ሀገራዊ የማንሰራራት ጉዞን የሚያፋጥኑ መሆናቸው ተገለጸ። በክልሉ ጳጉሜን 2 “የማንሰራራት ቀን”ን አስመልክቶ በግብርና፣ በመንገድ ትራንስፖርት፣ በማዕድንና ኢነርጂ፣ በከተማና መሰረተ ልማት እንዲሁም በኢንዱስትሪና በሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች የተከናወኑ ተግባራት ላይ የመስክ ምልከታ ተደርጓል። በተጨማሪም በተመዘገቡ ስኬቶችና በቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ የፓናል ውይይት ተካሂዷል። በፓናል ውይይቱ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት የክልሉ መንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ አስፋው ጎኔሶ እንደተናገሩት፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የህዝብን ተጠቃሚነት ያረጋገጡና ተጨባጭ ውጤቶች የተመዘገቡባቸው ተግባራት ተከናውነዋል። ያሉትን ጸጋዎች ወደ ውጤት ለመቀየር የተደረጉ ጥረቶች አዎንታዊ ውጤት ማምጣታቸውን አውስተው፤ ለአብነትም በግብርናው ዘርፍ የገበያውንና የኢንዱስትሪ ፍላጎቶችን መሸፈን የቻሉ ምርቶች መቅረባቸውን ተናግረዋል። ከግብርናው ባለፈ በመንገድ ልማት፣ በማዕድን ሀብትና በኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም እንዲሁም ተወዳዳሪነትን በማሳደግ ለበርካቶች የስራ ዕድል ከመፍጠር ባሻገር ለሀገር ኢኮኖሚ የበኩሉን ሚና እየተጫወተ መሆኑን አስረድተዋል። የልማት ስራዎች የማስፈጸም አቅም እያደገ መምጣቱን ጠቅሰው፤ በቀጣይም የተመዘገቡ ስኬቶችን በማስቀጠል ሀገራዊ የማንሰራራት ጉዞን ለማፋጠን የክልሉ መንግስት በላቀ ቁርጠኝነት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በከተሞችና መሰረተ ልማት ዘርፍ እየታዩ ያሉ አመርቂ ውጤቶችን ማጠናከር በልዩ ትኩረት የሚሰራበት መሆኑን ያነሱት አቶ አስፋው፤ በክልሉ የተያዙ ግቦች በተቀናጀ መልኩ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል ። አደጋዎችንም በራስ አቅም ለመቋቋም የተጀመሩና የተገኙ አበረታች ጥረቶችም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስረድተዋል። በተጨማሪም የአገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን የተገኙ ስኬቶችን ወደላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በልዩ ትኩረት በመስራት ሀገራዊ የማንሰራራት ጉዞን ለማጠናከር ይሰራል ብለዋል።   የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በክልሉ በኢኮኖሚና ማህበራዊ ዘርፎች እምርታዊ ለውጥ ያስገኙ ስኬቶ መመዝገባቸውን ገልጸዋል። በተለይም የግብርናውን አቅም ለመጠቀም የተደረገው ጥረት የነዋሪውን ተጠቃሚነት ያረጋገጠ ሲሆን፤ ለመስኖ እርሻ የተሰጠው ትኩረትና በእንስሳት ሀብት ልማት የተገኙት ስኬቶች አበረታች መሆናቸውን ነው የገለጹት። በክልሉ በተለያዩ ዘርፎች ሁለንተናዊ ስኬት እንዲመዘገብ የተደረጉ ጥረቶች ምቹ መደላድል መፍጠራቸውን በመግለጽ፤ በቀጣይም እነዚህ ተግባራት በላቀ ጥረት እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። የጳጉሜን ቀናትን መከበራቸው ከትናንትናው ስኬት በመማር ለቀጣይ ዓመት መነሳሳትን እንደሚፈጥር ገልጸው፤ ከንግግር ባለፈ በተግባር ለመፈጸም ቃላችንን አድሰን የምንነሳበት ነው ብለዋል።    
አፍሪካዊቷ የብልፅግና አብሪ ኮኮብ፤ የኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ ማንሰራራት ታሪካዊ እጥፋት
Sep 7, 2026 50
በመደመር መንግሥት እሳቤ የተቃኘው ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ኢትዮጵያ ለዘመናት ሲገጥማት የነበረውን የኢኮኖሚ ስብራት በማከም አዳዲስ የዕድገትና ብልጽግና ዕድሎችን ፈጥሯል። ሪፎርሙ የማክሮ ኢኮኖሚ ሚዛኖችን ከማስተካከል ባለፈ የምርት አቅምን ማሳደግ፣ ኢንቨስትመንትን ማበረታታት፣ የፋይናንስ ዘርፉን ማዘመንና የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማስፋት የሚያስችል መሠረት ገንብቷል። በሁለት ምዕራፎች እየተተገበረ ያለው የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያም የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ከነባር ችግሮች ወደ ዘላቂና የምርታማነት ዕድገት በማሸጋገር የዘርፎችን የማንሰራራት ጉዞ እያበሰረ ይገኛል። ይህም ኢትዮጵያ በ2016 ዓ.ም 8 ነጥብ 1 በመቶ፣ በ2017 ዓ.ም 9 ነጥብ 2 በመቶ ተከታታይ ጥቅል ሀገራዊ ዕድገት እንዲያስመዘግብ እንዲሁም በ2018 ዓ.ም 10 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት እንዲጠበቅ አስችሏል። በዘርፎች ሲታይም በ2017 ዓ.ም በጀት ዓመት ግብርና 7 ነጥብ 3 በመቶ፣ ኢንዱስትሪ 13 በመቶ እና አገልግሎት 7 ነጥብ 5 በመቶ ጥቅል ዕድገት በማስመዝገብ የዘርፎችን ቀጣይነት ያለው ማንሰራራት አመላካች ሆኗል። በተለይም በሁለት ምዕራፍ በተከፈለ መርሐ ግብር ተግባራዊ የተደረጉ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሐ ግብሮች የዘርፎችን እመርታዊ ውጤት በማላቅ የኢትዮጵያን ማንሰራራት እያፋጠኑ ናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ማጠቃለያ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባቀረቡት ሪፖርት እንዳሉት፤ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው ከተጠበቀው በላይ አመርቂ ውጤት አምጥቷል። የኢትዮጵያ በእመርታ የታጀበው የኢኮኖሚ ማንሰራራት ስኬት በአፍሪካ ፈጣን ዕድገት ካላቸው ግንባር ቀደም ሀገራት እንዳደረጋት አስታውሰዋል። ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያውም የማክሮ ኢኮኖሚ ስብራቶችን በማከም ከነባሩ የግብርና መር ክፍለ ኢኮኖሚ ወደ ብዝኅ ዘርፍ በማሸጋገር ጥራት ያለው ዕድገት እንድታስመዘግብ እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል። ይህም የኢኮኖሚ ማንሰራራትን በጽኑ መሠረት በማነጽ በሁሉም ዘርፍ የተቀናጀና ቀጣይነት ያለው የዕድገት ሽግግር የሚሳለጥበትን ሁኔታ እንደፈጠረ አብራርተዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረገው ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ የዕድገት ምዕራፍ ያሸጋገረ ነው ብለዋል። የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሐ ግብር ትግበራ ቁርጠኝነት አስተማማኝና ቀጣይነት ያለው ዕድገት እንዲመዘገብ ያስቻለ መሆኑን አስረድተዋል። ይህም አፍሪካዊት የብልጽግና ተምሳሌት ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በአሥር ዓመቱ የልማት ዕቅድ በበርካታ መመዘኛ ግቡን እየመታ መሆኑን እንደሚያመላክት አብራርተዋል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ በበኩላቸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ አመርቂ ውጤት ማስመዝገቡን ገልጸዋል፡፡ ለውጤቱም ገበያ መር የውጭ ምንዛሬ፣ የሞኒተሪ ፖሊሲ፣ የኢንቨስትመንት ሕግ፣ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች አስቻይ ምኅደር መፈጠሩ የዘርፎችን እመርታዊ የዕድገት ጉዞ ለማስፋት አስችሏል ብለዋል። የኢትዮጵያ አጠቃላይ እመርታዊ የኢኮኖሚ ዕድገት የማንሰራራት ጉዞም በዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ጭምር የተረጋገጠ ሐቅ መሆኑን አብራርተዋል። የኢኮኖሚ ምሁር ተወልደ ግርማ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሐ ግብሩ የዋጋ ግሽበትን በማርገብ የኑሮ ውድነት እንዳይባባስ ማድረጉን ገልጸዋል። ለአብነትም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በሚቀጥሉት አሥር ዓመታት ውስጥ በብዙ እጥፍ እንደሚልቅ የዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማትና የአሜሪካ ኢንቨስትመንት ባንኮች በጥናታቸው መተንበያቸውን አንስተዋል። ሌላኛው የኢኮኖሚ ምሁር ደረጀ ደጀኔ፤ የኢትዮጵያ ሁለንተናዊ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በሀገሪቱ ታሪክ ታይቶ የማይታወቅ የኢኮኖሚ መነቃቃትን የፈጠረ የፖሊሲ እርምጃ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የንግድና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ፍሰትን በማበረታታት የኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ የንግድ ሚዛን የሚያስጠበቅ የምርታማነትና ቀጣይነት ያለው የዕድገት ምኅደር መፍጠር እንደሚያስችል ገልጸዋል።  
በአማራ ክልል የተገነቡ ታላላቅ የልማት ፕሮጀክቶች የክልሉን ማንሰራራት በተግባር ያረጋገጡ ናቸው
Sep 7, 2026 50
ባህር ዳር፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ ታላላቅ የልማት ፕሮጀክቶች ተገንብተው መጠናቀቅ የክልሉን የማንሰራራትና የለውጥ ምዕራፍ በተግባር እንደሚያረጋግጥ ተገለጸ። ጳጉሜን-2 የማንሰራራት ቀን ተብሎ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎችየተከበረ ሲሆን በባህር ዳር ከተማም ቀኑ በፓናል ውይይትና በፎቶ ግራፍ አውደ ርይዕ ተከብሯል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጽህፈት ቤት ምክትል ሃላፊ አቶ አብደላ ኑሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በተለያዩ የልማት ሥራዎች የተመዘገቡ ውጤቶች የክልሉን የለውጥ ጉዞና ማንሰራራት የሚያረጋግጡ ናቸው። በተለይም የህዝብን የአገልግሎት አሰጣጥ ለማሳለጥ በሲቪል ሰርቪስ፣ በፀጥታ፣ በፍትህና መሰል ተቋማት የተከናወኑ የሪፎርም ሥራዎች ተጨባጭ ለውጥ አምጥተዋል ብለዋል። በከተሞች ልማት፣ በማዕድን ልማት፣ በግብርና፣ በንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት እና በማድረግና ቴክኖሎጂን በማስፋት አዳጊ ስራዎች መከናወናቸውንም አመልክተዋል። በይቻላል መንፈስ በክልሉ ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ ታላላቅ የልማት ፕሮጀክቶችን ገንብቶ ማጠናቀቅ የክልሉን የለውጥና የማንሰራራት ጉዞ ማሳያ ናቸው ብለዋል። የክልሉ ማዕድን ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ታምራት ደምሴ በበኩላቸው በማዕድን ዘርፍ እየተመዘገበ ያለው ተጨባጭ ውጤት የሀገርና የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያሳድግ ነው። ዘርፉ ለዘመናት ትኩረት ተነፍጎት መቆየቱን አስታውሰው፤ በአሁኑ ወቅት መንግስት ለብዘሀ ዘርፍ በሰጠው ትኩረት ማዕድን የኢኮኖሚው አንድ ምሰሶ ሆኖ በትኩረት እየተሰራበት ይገኛል ብለዋል።   ባለፉት ጊዜያት 50 ማዕድናትን በጥናት የመለየት ሥራ መሰራቱን ገልጸው የክምችት ግመታና የፍለጋ ሥራም እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ 357 ኪሎ ግራም ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ እና 28 ሺህ ኪሎ ግራም ኦፓል ለውጭ ገበያ እንደቀረበና ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ3 ሺህ 500 በላይ የውሃ ተቋማትን ገንብቶ ለአገልግሎት በማብቃት ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ህዝብ የንፁህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የገለፁት ደግሞ የክልሉ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ጥላሁን ሽመልስ ናቸው። በ2019 በጀት ዓመትም የንፁህ መጠጥ ውሃ ተደራሽነትን ለማሳካት ከ3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ብር በጀት ተመድቦ ወደ ስራ ተገብቷል ብለዋል። በክልሉ የንፁህ መጠጥ ውሃ እና የአማራጭ ሃይል አቅርቦትን በገጠርና በከተማ ተደራሽ የማድረጉ ሥራ ከመቸውም ጊዜ በላይ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በመድረኩ የክልሉ የተለያዩ ቢሮዎች አመራሮች እና ባለሙያዎች የተሳተፉ ሲሆን የልማት ሥራዎችን የሚያስቃኝ የፎቶ አውደ ርዕይም ተካሄዷል።    
የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን የመኖሪያ ቤት ግንባታ ርዕይ፤ የመደመር መንግሥት የግንባታ ዘርፍ የማንሰራራት ስንቅ
Sep 7, 2026 65
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጳጉሜ 4 ቀን 2017 ዓ.ም በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ምረቃ ወቅት የኢትዮጵያን የብልጽግና ፍኖት የሚያበስሩ ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን አብስረዋል። የጉባ ብስራቶችም የኢትዮጵያን ኃይል፣ ኢንዱስትሪ፣ አቪዬሽን፣ ማዕድንና ከተማ ልማት ልህቀት በማጎልበት የሀገርን መቻልና መርህ በተግባር የሚያረጋግጡ ናቸው። የአዲሱ የቢሾፍቱ ሜጋ አየር ማረፊያ፣ የነዳጅ ዘይት ማጣሪያ፣ ሰላማዊ የኒውክሌር ማብላያ፣ የተፈጥሮ ጋዝ ፋብሪካ፣ የማዳበሪያ ፋብሪካ እና የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክቶች ናቸው። የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት ርዕይም የመደመር መንግሥት የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ የግንባታ ዘርፍ የማንሰራራት ጉዞ መሠረት ስንቅ ሆኗል። ለዚህም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ነሐሴ 28 ቀን 2018 ዓ.ም በኢትዮጵያ የመጀመሪያውን የተለየ የቤት መግዣ ብድር መልሶ ማጠናከሪያ ኩባንያ ለማቋቋም የሚያስችለውን ታሪካዊ የትብብር ማዕቀፍ ይፋ አድርገዋል። በብሔራዊ ባንክ እና በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን መካከል የተደረሰው ስምምነትም አጋርነትን በማጠናከር በተመጣጣኝ ዋጋ የሚገነቡና ኢትዮጵያውያንን ክብር የጠበቁ ቤቶችን መገንባት ያስችላል። በተለይም የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶችን ግንባታ በማሳካትና በፋይናንስ ሥርዓቱ ውስጥ የግል ዘርፉን ተሳትፎ ለማስፋት የተቀመጠውን ግብ የሚያሳካ ወሳኝ እርምጃ ነው ብለዋል። በባንክ ዘርፉም የጥሬ ገንዘብ ፍሰት አለመመጣጠንን የሚቀርፍና በመላው ኢትዮጵያ ተደራሽ የሚሆን የቤት መግዣ ብድር ፋይናንስን የሚያስገኝ እንደሚሆን አስረድተዋል። ሕዳሴ ግድብን እውን ያደረገው የኢትዮጵያውያን ጥንካሬና አንድነት አሁንም በዚሁ የመኖሪያ ቤቶች ልማት ፕሮጀክት ላይ እየተደገመ ይገኛል። ኢትዮጵያውያን በራሳቸው አቅም በዓባይ ላይ ሕዳሴን እውን እንደአደረጉ ሁሉ የዜጎቿን የመኖሪያ ቤት ጥያቄም በራሷ ጥረትና ትብብር ለመፍታት ጉዞዋን እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል። ለዚህም በመጪዎቹ አምስትና ስድስት ዓመታት በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ምረቃ ወቅት 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ቤቶችን በመገንባት ለዜጎች ለማስተላለፍ ዕቅድ መያዙን አብስረዋል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ እያንዳንዱ የከተማና መሠረተ ልማት ግንባታ ሰው ተኮርነትንና ፍትሐዊነትን ማዕከል ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በከተማና ገጠር ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው፣ ኢትዮጵያውያንን ክብር የሚመጥኑ የመኖሪያ ቤቶችና መሠረተ ልማቶች ተገንብተው ለአገልግሎት እየበቁ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የከተማና ገጠር ልማት ውጤቶችም ከሚያበረክቱት ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ባሻገር በሀገር ገጽታ ግንባታ ጉልህ ፋይዳ እያበረከቱ መሆናቸውን ተናግረዋል። የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ የተፈጠረው አስቻይ ምኅዳር ለቤት ልማት ወሳኝ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ የፈጠረውን ዕድል በመጠቀም በሚቀጥሉት አምስትና አስርት ዓመታት የከተሞችን የመኖሪያ ቤት እጥረት ለማቃለል በትኩረት እንደሚሠሩ አስረድተዋል። የኦቪድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዮናስ ታደሰ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ የሚያሳድግ ምኅዳር ተፈጥሯል ብለዋል። በዚህም በአዲስ አበባ ከተማ የዜጎችን የመኖሪያ ቤት አቅርቦት ፍላጎት ምላሽ የሚሰጡ ዘመናዊ ቤቶችን በመገንባት ለተጠቃሚዎች እያስተላለፉ እንደሚገኙ አስረድተዋል።  
በብዝሀ ዘርፍ የኢኮኖሚ መስኮች የተገኙ ተጨባጭ ስኬቶች የኢትዮጵያን ማንሰራራት አመላካች ናቸው - የምጣኔ ሀብት ምሁራን
Sep 7, 2026 102
ቦንጋ፣ ጳጉሜን 2/2018(ኢዜአ)፦ በብዝሀ ዘርፍ የኢኮኖሚ መስኮች እየተመዘገቡ ያሉ ተጨባጭ ስኬቶች የኢትዮጵያ ማንሰራራትና በጽኑ የእድገት መሠረት ላይ መቆሟን የሚያመለክቱ ናቸው ሲሉ የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሀብት ምሁራን ገለጹ። ኢትዮጵያ ከነጠላ የኢኮኖሚ እድገት ወጥታ በብዝሀ ዘርፍ ኢኮኖሚ ባከናወነቻቸው ተግባራት በተለያዩ መስኮች ፈጣን እድገት በማስመዝገብ የማንሰራራት ጉዞ ላይ ትገኛለች። ከግብርና መር እድገት ተላቃ ለብዘሃ የኢኮኖሚ ዘርፍ በሰጠችው ትኩረትና በመደመር መንግስት በተወሰዱ የማሻሻያ እርምጃዎች እየተመዘገቡ ያሉ ተጨባጭ ውጤቶች የሀገሪቷን ቀጣይ ብሩህ ተስፋ የሚያሳዩ ናቸው። በጉዳዩ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የቦንጋ ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሀብት ምሁራን ኢትዮጵያ አሁን እየሄደችበት ያለው የማንሰራራት ጉዞ ያለመችው ብልፅግና ላይ እንደምትደርስ አመላካች መሆኑን ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የምጣኔ ሀብት መምህሩ ጌትነት ገዛሃኝ (ዶ/ር) እንደገለጹት ኢትዮጵያ ከድህነት ታሪክ ተላቃ ወደ ቀደመ ክብሯና ገናናነቷ እንድትመለስ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርሙ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ ነው። በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በቱሪዝም፣ በአረንጓዴ አሸራ፣ በሜጋ ፕሮጀክቶችና በሌሎችም የኢኮኖሚ መስኮች የተከናወኑ ተግባራት መጪውን ትውልድ ጭምር ታሳቢ ያደረጉና ሁለንተናዊ ብልጽግናን የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል። "የኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፈ የነበሩ ማነቆዎችን በመፍታት ሥራ ያቆሙ በርካታ ፋብሪካዎች መልሰው ወደ ሥራ እንዲገቡ ማድረጉን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ በንቅናቄው የሀይል፣ የገንዘብ ብድርና የጥሬ እቃ አቅርቦት በሰፊው መሰራቱ ዘርፉ ከፍተኛ መሻሻል እንዲያሳይ ማስቻሉን ጌትነት ( ዶ/ር) ተናግረዋል። በዚህም ኢትዮጵያ ከውጭ ታስገባ የነበረቸውን በርካታ ምርቶች በሀገር ውስጥ በማምረት የውጭ ምንዛሬን ለማዳን ከመቻሉ በላይ የኤክስፖርት ምርቶች በመጠንና ጥራት አድገዋል ብለዋል። የሕዳሴው ግድብ ለኢንዱስትሪዎችና ሌሎችም ዘርፎች በቂና አስተማማኝ የሀይል ምንጭ መሆኑን ጠቁመው፣ ባለፉት ዓመታት በዘርፉ በተከናወኑ ሥራዎች የተገኙ ተጨባጭ ውጤቶች የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞን ያሳያሉ ሲሉ ገልጸዋል።   ሌላኛው በዩኒቨርሲቲው የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ ዲን እና የምጣኔ ሀብት መምህር ብዙአየሁ አየለ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በመደመር መንግስት በግብርናውና በኢንዱስትሪ ሴክተሮች የመጣው ተጨባጭ እድገት የሀገርን ማንሰራራት ያሳያሉ። ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሜካናይዜሽን እርሻና ቴክኖሎጂዎችን በሰፊው ሥራ ላይ ማዋል በመቻሉ በተለይ የስንዴ ምርትን ከሀገር ውስጥ ባለፈ ወደ ውጭ ለመላክ መቻሉን ተናግረዋል። በኢንዱስትሪው ዘርፍ የተወሰዱ እርምጃዎች ዘርፉን በከፍተኛ መጠን በማነቃቃት የማምረት አቅምን እያጎለበተ መሆኑንም ገልጸው፣ ዘርፉ ለዜጎች ከፍተኛ የሥራ ዕድል እየፈጠረ መሆኑንም አንስተዋል። ቀደም ሲል ቱሪዝምን ጨምሮ ትኩረት ተነፍጎት የቆየውን የአገልግሎት ዘርፍ ውጤታማ ለማድረግ በመንግስት የተወሰዱ ትልልቅ እርምጃዎች እንዲሁም የተገነቡና በሂደት ላይ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች የሀገርን ማንሰራራት ያፋጥናሉ ብለዋል።
የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ማንሰራራት ያረጋገጡ ስኬቶች ተመዝግበዋል
Sep 7, 2026 79
ወላይታ ሶዶ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ በየዘርፉ የተመዘገቡ ስኬቶች የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ያረጋገጡና የሀገርን ማንሰራራት ያሳዩ መሆናቸውን ምሁራን ተናገሩ። ኢዜአ ያነጋገራቸው የዩኒቨርሲቲው ምሁራን እንዳሉት በግብርና፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በማዕድንና በሌሎች ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶች አበረታች ናቸው፡፡ በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ በቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል የኢኮኖሚክስ ትምህርት መምህርና ተመራማሪ ሰለሞን ከበደ (ዶ/ር) እንዳሉት፣ በመደመር መንግሥት የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ የመልማት አቅምን በመለየትና በቅንጅት በመስራቱ ውጤት እየተመዘገበ ነው። ይህም የተጀመረውን ብልጽግና ጉዞ በማሳካት አስተማማኝ ኢኮኖሚን ለመገንባት መሰረት የሚጥል መሆኑን ተናግረዋል። ቀደም ባሉት ጊዜያት በግብርና ላይ ብቻ አተኩሮ የነበረውን ኢኮኖሚ ወደ ብዝሀ ዘርፈ መቀየሩ ለዜጎች የሥራ ዕድል በማስፋትና ዘላቂ ማህበራዊና የኢኮኖሚ ዕድገት ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ለዚህም በግብርናው፣ በኃይል አቅርቦት፣ በኢንዱስትሪ ልማት፣ በቱሪዝም፣ በማዕድን ልማት፣ በአገልግሎት ዘርፎች እንደ ሀገር ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ እየተመዘገቡ ያሉ ውጤቶች የሀገርን ማንሰራራት የሚያረጋግጡ መሆናቸውን ተናግረዋል።   በዩኒቨርሲቲው ግብርና ኮሌጅ የሰብል ልማት ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ደረጀ ሻንካ (ዶ/ር) ግብርናን ለማዘመን የተከናወኑ ተግባራት ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር አድርጓል። ይህም የዜጎችን የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ካለው ፋያዳ በተጨማሪ ለኢንዱስትሪው ግብእት በበቂ ሁኔታ ለማቅረብ አይነተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይ በስንዴ ልማት የተመዘገበው እድገት ምርቱን ከሀገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ወደውጭ መላክ መቻሉ የኢትዮጵያን ማንሰራራት በተጨባጭ ያሳየ ነው ብለዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ዜጎች በአነስተኛ ሥፍራ ላይ በማምረት የምግብ ዋስትናቸውን የሚያረጋግጡበትን አቅም እየፈጠሩ መምጣታቸውንም ዶክተር ደረጀ ጠቅሰዋል። ከግብርና ልማት ስራው በተጨማሪ በማዕድን፣ በኮንስትራክሽንና ሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች እየተገኙ ያሉ ውጤቶች ሀገሪቱ ዳግም በመነሳት አዲስ የእድገት ከፍታ ላይ እንደምትደርስ የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በግንባታ ሂደት ላይ ያሉ ትላልቅ ሀገራዊ ግዙፍ ፕሮጀክቶችም የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ እውን እየሆነ መምጣቱንማሳያዎች ናቸው ብለዋል።
በኦሮሚያ ክልል ባለፉት አመታት የተሰሩ የልማት ስራዎች ወደ ከፍታ የሚደረገውን ጉዞ ያረጋገጡ ናቸው
Sep 7, 2026 66
ነቀምቴ፣ ጳጉሜን 2/2018(ኢዜአ) ፡-በኦሮሚያ ክልል ባለፉት አመታት የተሰሩ የልማት ስራዎች ወደ ከፍታ የሚደረገውን ጉዞ ያረጋገጡ ናቸው ሲሉ የኦሮሚያ ማዕድን ልማት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ነመራ ገበየሁ (ዶ/ር) ገለጹ። ጳጉሜ 02 የማንሰራራት ቀን በኦሮሚያ ክልል ደረጃ በነቀምቴ ከተማ በተለያዩ መርሃግብሮች ተከብሯል።   ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች፣ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተግባራት፣ የልማት ፕሮጀክቶች ጉብኝትና የፓናል ውይይት ደግሞ ከተካሄዱት ሁነቶቹ መካከል ናቸው። የኦሮሚያ ማዕድን ልማት ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ነመራ ገበየሁ(ዶ/ር) በመድረኩ ላይ በመገኘት ባስተላለፉት መልዕክት፣ በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ዓመታት የቤተሰብ እና የማህበረሰቡን ብልፅግና ለማረጋገጥ በተሰሩ ስራዎች ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል። በተለይም የክልሉን የኢኮኖሚ አቅም በማጎልበት በርካታ ስራዎች መሰራታቸውን አንስተው፣ በዚህም የኢንዱስትሪ፣ የግብርና፣ የንግድ እና የአገልግሎት ዘርፎችን በማስተሳሰር ውጤታማ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። ለአብነትም የወለጋ ዞኖችን የልማት በር ለማድረግ እንቅስቃሴዎች እየተፋጠኑ መሆናቸውን ገልጸው፤ የተገኙት ውጤቶችም አካባቢውን ወደ ታቀደው ከፍታ ለማሻገር እንደሚረዱ ጠቁመዋል። የማህበረሰቡን ጥያቄዎች ለሚመልሱ ሥራዎች ቅድሚያ በመስጠት፣ ፈተናዎችን ወደ መልካም አጋጣሚ በመቀየር፣ ፕሮጀክቶችን አስጀምሮ ከመጨረስ ባሻገር ተስፋን በተግባር ለመፍጠር እየተሠራ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ህብረተሰቡ መንግሥት የጀመራቸውን የከፍታ ሥራዎች በማገዝ የልማት እንቅስቃሴዎች በፍጥነትና በጥራት እንዲጠናቀቁ የበኩሉን መወጣት እንዳለበትም አስገንዝበዋል።   የነቀምቴ ከተማ ከንቲባ አቶ መሠረት ኃይሉ በበኩላቸው፣ "ነቀምቴ ከተማ በፈጣን የእድገት ጎዳና ላይ የምትገኝ ከተማ ናት ብለዋል። በከተማው በተለይም በኮሪደር ልማት የተሠራው ሥራ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባሻገር፣ የነዋሪዎችን ሕይወት ያዘመነ መሆኑን ገልጸዋል። በከተማው እስካሁን በተከናወኑ የልማት ሥራዎች የሕብረተሰቡ ተሳትፎ የጎላ እንደነበረ የገለጹት ከንቲባው፤ በቀጣይም ይህ ተሳትፎ ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው አብራርተዋል። ከተማዋን ወደ ላቀ ከፍታ ለማሸጋገር ሁሉም አካላት በመተባበር የተጀመሩ የልማት እንቅስቃሴዎችን ጠንክረን መስራት አለብን ብለዋል።   በመርሐ ግብሩ ላይ የክልሉና የዞኑ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችን ጨምሮ የነቀምቴ ከተማና የአካባቢው ነዋሪዎች ተሳታፊ ሆነዋል።  
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በራስ የመተማመን መንፈስን በማጎናፀፍ የኢኮኖሚ ማንሰራራት ጉዞን እያፋጠነ ነው - አረጋዊ በርሔ (ዶ/ር) 
Sep 7, 2026 297
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ) ፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በራስ የመተማመን መንፈስን በማጎናጸፍ የኢኮኖሚ ማንሰራራት ጉዞን እያፋጠነ መሆኑን የህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያውያን መሐንዲሶች፣ የገንዘብ ምንጮችና ግንበኞች ሆነው የገነቡት ታላቁ ህዳሴ ግድብ ሚያዚያ 24 ቀን 2003 ዓ.ም በጉባ ተራሮች ግርጌ መሰረት መጣሉ ይታወሳል። ከታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ማስጀመሪያ ማግስትም ዓባይን ለሺህ ዓመታት በብቸኝነት ስትጠቀም የቆየችው ግብፅና አጋሮቿ ፕሮጀክቱን ለማደናቀፍ ጥረት አድርገዋል። ኢትዮጵያውያን በታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ሂደት ለ14 ዓመታት ባደረጉት ተጋድሎ ዓባይ ለእናቱ በረከት የሚሆንበት ብስራት በጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም ተሰምቷል። ዓባይ ተገርቶ የኤሌትሪክ ኃይል የማመንጨት ተግባሩንም ጀምራል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በምርቃቱ ወቅት የጎረቤት ሀገራት መሪዎችን፣ ቀጣናዊና አህጉራዊ ተቋማት ኃላፊዎችን ጋብዘው ታላቁ ሕዳሴ ግድብን ሲመርቁ ኢትዮጵያ በዓባይ ላይ ከውስጥ የተሻገረ የማንሰራራት ጅማሮን ማብሰራቸውም ይታወሳል። ኢትዮጵያውያን የሀገራቸውን የማንሰራራት ጉዞ የሚያጎናጹፍ ግዙፍና አስተሳሳሪ ፕሮጀክቶችን በራሳቸው አቅም ብቻ መገንባት እንደሚችሉ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ በድል መጠናቀቅ ለዓለም ሕዝብ አሳይቷል። ይህም ኢትዮጵያን የታዳሽ ኃይል አቅም በመገንባት የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ አቅጣጫ ላይ ታሪክ ቀያሪ ድንቅ የልማት ውጤት ሆኖ በታሪክ ድርሳናት ተመዝግቧል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሔ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ በኢትዮጵያውያን የራስ አቅም የተገነባ የመተባበር ውጤት ሆኖ የተመዘገበ ነው። ኢትዮጵያውያን በታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ የነበራቸው ሁለንተናዊ ተሳትፎ በቀጣይም ያለአንዳች የውጭ እርዳታና ብድር ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በራስ አቅም መገንባት እንደሚችሉ ትምህርት የሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የሀገሪቱን በራስ የመተማመን መንፈስ ያነጸና የኢኮኖሚ ማንሰራራት ጉዞዋን እያፋጠነ የሚገኝ ግዙፍ አህጉራዊ የልማት ውጤት መሆኑንም አስረድተዋል። ግድቡ ከብዙ ማዕዘናት ሲታይም የሀገሪቱን ዘመናዊ የልማት ጉዞ ወደ አዲስ ከፍታ በማሸጋገር አዲስ የመቻል መንፈስን ያጎናጸፈ ወሳኝ መሠረተ ልማት መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም የሕዳሴው ግድብ ከኢትዮጵያ ባሻገር የምሥራቅ አፍሪካ ሀገራትን በኃይል በማስተሳሰር በጋራና በትብብር የማደግ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ወሰን ተሻጋሪ የኤሌክትሪክ ኃይል መሠረተ ልማትም ኢትዮጵያ የጋራ ብልፅግናን በማሳለጥ ቀጣናዊና አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደትን ለመፍጠር ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር ያስመሰከረ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም ኢትዮጵያ ወሰን ተሻጋሪ ግዙፍ ወንዞቿን በማልማት የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥኑ ግዙፍ የኃይል ማመንጫና የመስኖ ግድቦችን መገንባት እንደሚጠበቅባት አስገንዝበዋል። ለዚህም ሕዳሴ ግድብ ለኢትዮጵያና ሕዝቦቿ የፈጠረላቸውን በራስ መተማመን በመጠቀም የኢኮኖሚ ዕድገትና ብልፅግናን ማፋጠን እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል።
ማዕከሉ እንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በስፋት እና በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረበ ነው
Sep 7, 2026 95
አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 2/2018(ኢዜአ)፦መጪውን በዓል ምክንያት በማድረግ የእንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በስፋት እና በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረበ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የእንስሳት ልማትና ልህቀት ማዕከል ገለጸ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽን ሥር የሚገኘው የእንስሳት ልማትና ልህቀት ማዕከል፣ መጪውን በዓል ምክንያት በማድረግ የገበያ ዋጋን ለማረጋጋት የእንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረበ መሆኑን አስታውቋል፡፡ የማዕከሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ አሌክስ ደመቀ እንደገለጹት፤ ማዕከሉ አርሶ አደሮችን ለማቋቋም፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና ገበያ ለማረጋጋት ነው የተቋቋመው፡፡ በአሁኑ ወቅት የደለቡ በሬዎችንና የእንስሳት ተዋጽኦዎችን በማዕከሉ እና በተለያዩ ቦታዎች በማቅረብ ላይ እንደሚገኝም ነው የገለጹት፡፡ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በተዘጋጁ ባዛሮች ላይም ከ350 ሺህ በላይ እንቁላል ማቅረቡን ጠቅሰው ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡ በማዕከሉ የተሰማሩ አምራቾች በበኩላቸው መንግሥት ባመቻቸላቸው ዕድል ተጠቅመው ምርቶቻቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል።   የእንቁላል አምራች አበራሽ ንጉሤ እንዳሉትም ምርታቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረቡ መሆናቸውን ገልጸዋል። የወተት ተዋጽኦ አምራቿ ወይዘሮ የሺወርቅ ዳኛቸው ለበዓሉ የሚሆኑ እንደ ቅቤና አይብ ያሉ ምርቶችን ከውጭው ገበያ በቅናሽ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረቡ መሆናቸውን ገልጸዋል።   ማዕከሉ ከተቋቋመበት ከ2015 ዓ.ም መጨረሻ ጀምሮ በእንቁላል ጣይ ዶሮ እርባታ፣ በእንስሳት ማድለብና በወተት ላም እርባታ ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ ይገኛል።    
ለሀገራዊ የኢኮኖሚ ማንሰራራት ሚናውን እያጎለበተ የሚገኘው - የማዕድን ዘርፍ
Sep 7, 2026 151
አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 2/2018(ኢዜአ)፦መንግስት ለማዕድን ዘርፍ ልማት የሰጠው ልዩ ትኩረት እና እየተገኘ ያለው ውጤት ለሀገራዊ የኢኮኖሚ ዕድገቱ ማንሰራራት የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ኢትዮጵያ በርካታ የማዕድን ሀብት ከሚገኝባቸው ሀገራት መካከል አንዷ ብትሆንም ቀደም ባሉት ጊዜያት ሀብቱን በማልማት ለሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ከማድረግ አንጻር አመርቂ አልነበረም። ባለፉት ዓመታት መንግሥት በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርም አጀንዳ ማዕድንን አንዱ መሠረታዊ የኢኮኖሚ ልማት ምሰሶ በማድረጉ ዘርፉ ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ምቹ ምህዳር ተፈጥሯል። የማዕድን ሚኒስትር ዴኤታ ብርሃኔ ያዴሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በመደመር መንግሥት በማዕድን ዘርፍ የውጭና የሀገር ውስጥ ባለሀብቶች በኢንዱስትሪው እንዲሰማሩ የፖሊሲ እና ምቹ ምህዳር መፍጠር ተችሏል። የማዕድን ዘርፍ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለተኪ ምርት ዕድገት እና የውጭ ምንዛሬን ለማዳን በርካታ ፋይዳዎች እንዳለው አንስተው፤ ባለፉት አመታት ለዘርፉ ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ ተጨባጭ ውጤቶች ተገኝተዋል ብለዋል። የውጭና የሀገር ውስጥ ባለሀብቶችን በስፋት በዘርፉ ማሰማራት የሚያስችሉ አጋዥ የማዕድን ፖሊሲና ህግጋት ተሻሽለው ለማጸደቅ በሂደት ላይ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። ቀደም ሲል ማዕድናት በጥሬው ወደ ውጭ ይላኩ እንደነበር አንስተው በአሁኑ ወቅት እሴት ጨምሮ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ማቅረብ ላይ ትኩረት መደረጉንም ገልጸዋል። ለአብነትም በወርቅ፣ በድንጋይ ከሰል፣ ኦፓልና ሌሎች ጌጣጌጦች እሴት ተጨምሮባቸው ለውጭ ገበያ የሚቀርቡበት አሰራር በመፈጠሩ ስኬቶች ተመዝግበዋል ብለዋል። ባለፉት አራት ዓመታት በወርቅ ዘርፍ የውጭ ምንዛሬ ግኝት ላይ ከፍተኛ ስኬት መገኘቱን አንስተው፤ የወርቅ ማጣሪያ በሀገር ውስጥ እንዲገነባ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቁመዋል። የወርቅ ምርት በ2015 ዓ.ም ከነበረበት 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቶን በ2018 ዓ.ም ወደ 44 ሚሊዮን ቶን ማደጉንና የውጭ ምንዛሬ ግኝቱም ከ196 ሚሊዮን ዶላር ወደ 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ማደጉን ተናግረዋል፡፡ በሲሚንቶ ምርትም እንዲሁ ባለፉት አምስት ዓመታት ከ6 ነጥብ 2 ሚሊዮን ቶን ወደ 10 ነጥብ 4 ሚሊዮን ቶን በማደግ ከፍተኛ እመርታ ማሳየቱን ገልጸዋል። የድንጋይ ከሰል ምርት ቀደም ሲል በጥሬው ይቀርብ እንደነበር አስታውሰው አሁን ላይ እሴት ተጨምሮበት ወጥ በሆነ ጥራት ለሲሚንቶ ፋብሪካዎች ግብዓት እስከ 75 በመቶ መሸፈን የሚያስችል አቅም መፈጠሩን ጠቅሰዋል። በሌላ በኩል ቀደም ሲል የሴራሚክ ምርት በአብዛኛው ከውጭ ይገባ እንደነበር አውስተው አሁን ላይ መንግስት ለዘርፉ ትኩረት ሰጥቶ በመስራቱ በሀገር ውስጥ የማምረት አቅም አድጓል ብለዋል። በዚህም በሴራሚክ ምርት የሀገር ውስጥ ፍላጎትን መሸፈንና ለግዥ ይወጣ የነበረን የውጭ ምንዛሬ ማዳን መቻሉን ጨምረው ገልጸዋል።        
በግብርናው ዘርፍ እየተመዘገበ ያለው ዕመርታዊ ለውጥ የኢትዮጵያ የማንሰራራት ዘመን ብስራት ነጋሪ ነው
Sep 7, 2026 326
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ)፦ በክልሎች ግብርናውን በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ሁለንተናዊ ዕድገት ለማምጣት የተጀመረው ጥረት የማንሰራራት ዘመን ብስራት ነጋሪ መሆኑን የተለያዩ ክልሎች የግብርና ቢሮ ኃላፊዎች ገለጹ። ኢትዮጵያ ግብርናውን በመካናይዜሽን፣ በኩታ ገጠም እርሻ፣ እንዲሁም ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ ግብዓቶችን በስፋት በማቅረብ በግብርናው ዘርፍ ምርትና ምርታማነት ማሳደግ ችላለች። የአሰራር ሥርዓቶችን በማዘመንና እንደ ሰው ሰራሽ አስተውሎት ዓይነት ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂ በመጠቀም እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ ማሳካት የሚያስችል ውጤት ተመዝግቧል። ግብርናው ለኢኮኖሚያዊ ማንሰራራትና ለገጠር መዋቅራዊ ሽግግር ገንቢ ሚና መወጣት የሚችልበትን አቅም ፈጥሯል። በኢትዮጵያ ግብርናውን በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ሁለንተናዊ ዕድገት ለማምጣት የተጀመረው ጥረት የማንሰራራት ዘመን ብስራት ነጋሪ ነው። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ዑስማን ሱሩር ለኢዜአ እንዳሉት፤ መሬት፣ ጊዜ፣ ጉልበት እና ሀሳብን አቀናጅቶ በመጠቀም በሰብል ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ለውጥ መጥቷል። በዚህም በክልሉ በ2018 ወደ 1 ነጥብ 28 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በሰብል በመሸፈን፤ አጠቃላይ የሰብል ምርት መጠኑን ከ161 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ማድረስ ተችሏል ብለዋል። ከዚህም ባለፈ የሰብል ብዝሃነትን በማስፋት ከውጭ የሚገባውን ምርት የሚተኩ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ማምረት መጀመራቸውን ገልጸዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የግብርና ቢሮ ኃላፊ ማስረሻ በላቸው፤ በክልሉ "የማይታረስ መሬት ሊኖር አይገባም" በሚል በድግግሞሽ የሚታረሰውን መሬት ከ560 ሺህ ሄክታር ወደ 801 ሺህ ሄክታር በማሳደግ የኢትዮጵያን የማንሰራራት ዘመነ ለማብሰር መሰረት የሚጥሉ ውጤቶች መመዝገባቸው ገልጸዋል። በሆርቲካልቸር ልማት ከ41 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን በመግለጽ፤ ከ61 ሺህ ቶን በላይ ቡና ለዓለም ገበያ በማቅረብ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ተገኝቷል ብለዋል። በሌማት ትሩፋት ሥራዎችን ለማጠናከር የመኖ ማሽኖች ተከላ፣ የዓሳ ዕርባታ ማዕከላት ግንባታ፣ የዶሮ ማቆያና መሰል ማስፋፊዎችን እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ የምክትል ቢሮ ኃላፊ አጀበ ስንሻው በበኩላቸው፤ በክልሉ የግብርና ሜካናይዜሽን በማስፋት 1 ነጥብ 4 ሚሊዬን ሄክታር መሬት በትራክተር ይታረሳል ብለዋል። ለአርሶ አደሩ 7 ነጥብ 1 ሚሊዬን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ እና ከ 310 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር በማቅረብ የአቅርቦትን ማሻሻልና የታቀደውን የግብርና ግብዓት ማሳካት መቻላቸውን ገልጸዋል። በኩታ ገጠም እርሻ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ፣ ለሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎች ግብዓት ማቅረብ እና ለውጭ ገበያ የሚቀርበን ምርት ማሳደግ የሚያስችል ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል።      
ኢትዮጵያ የንጹህ ኃይል ልማቷን አጠናክራ ትቀጥላለች - ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ
Sep 7, 2026 345
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የንጹህ ኃይል ልማቷን አጠናክራ በመቀጠል ለጎረቤት ሀገራት የምታቀርበውን የኃይል መጠን ለማሳደግ እየሰራች መሆኑን ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ገለጹ። ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች ዱባይ እየተካሄደ ባለው ዓመታዊው ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ጉባኤ (AIM Congress) ላይ ንግግር አድርገዋል።   ፕሬዝዳንት ታዬ ለታዳሚዎች ባስተላለፉት መልዕክት፤ ጉባኤው የዓለም ኢኮኖሚ መዋቅር በመሰረታዊነት እየተለወጠና የቴክኖሎጂ ለውጦች አጠቃላይ ሁኔታዎችን እየቀየረ ባለበት ጊዜ መካሄዱ ጠቃሚ ያደርገዋል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት ተለዋዋጭ የጂኦ ፖለቲካ ሁኔታዎች የዓለምን የንግድ የእሴት ሰንሰለት እየወሰነ መምጣቱን ገልጸው፤ እነዚህ አዲስ ክስተቶች በማደግ ላይ ላሉ ሀገሮች በተለይም ለአፍሪካ ካመጡት ችግር ባልተናነሰ ወደ ውስጥ ለመመልከት ዕድል መፍጠሩን ጠቅሰዋል። ይህንንም ተከትሎ የአፍሪካ አገራት በአፍሪካ ኅብረት በኩል የዚህ ተለዋዋጭ ዓለም ክስተት ተመልካች ሳይሆኑ ዋነኛ ተሳታፊና ሥርዓት ገንቢ አካል ለመሆን የጋራ መግባባት መደረሱን ተናግረዋል። በተለይም ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት እየተገበረቻቸው ያሉትን ተከታታይ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ፕሮግራሞች ከዚህ አኳያ የተቃኙ መሆናቸውን አብራርተዋል። ፕሬዝዳንት ታዬ እንደገለጹት፤ አፍሪካ ዘላቂነት ያለው ኢኮኖሚ እንድትገነባ ያላትን የስትራቴጂክ ኢንቨስትመንት ዕድሎች አሟጣ ለመጠቀም አምስት ዋና ዋና ጉዳዮችን ማከናወን ይጠበቅባታል። አንደኛ በአፍሪካ የጋራ የኢንዱስትሪ ትራንስፎርሜሽን ለማምጣት በንጹህ የኤሌትሪክ ኃይል ማስፋፋት ላይ ትኩረት ሊያደርጉ እንደሚገባ ጠቅሰው፤ ሀገሮች በተለይም ከንፋስ፣ ከፀሐይ፣ ከአንፋሎትና ከኃይድሮ ኤሌክትሪክ ልማት ላይ ትኩረት ማድረግ እንዳለባቸው ገልጸዋል። ኢትዮጵያም የንጹህ የኃይል አማራጭን እንደ ሀገራዊ ሃብት ብቻ ሳይሆን ለፈጣን የኢኮኖሚ እድገት መሰረት አድርጋ ትወስደዋለች ሲሉ ፕሬዝዳንቱ አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ከንጹህ ሃይል ብቻ 60 ሺህ ሜጋ ዋት የኤሌትሪክ ሃይል የማመንጨት አቅም እንዳላት ገልጸው፤ እኤአ 2030 ኢትዮጵያ 15 ሺህ ሜጋ ዋት ለማመንጨት እቅድ እንዳላት ተናግረዋል። በዚህም ለምስራቅ አፍሪካና ለሌሎች አገሮች የሚቀርበውን የኃይል አቅርቦት ለማሳደግ እንደምትሰራም ጠቁመዋል። በሁለተኛ ደረጃ የአፍሪካ አገራት በግብርና ዘርፍ ላይ መሥራት እንዳለባቸው ተናግረው፤ ኢትዮጵያ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በተለይም በስንዴ ምርት ዘርፍ ያስመዘገበችውን እመርታ በተሞክሮ ለታዳሚው አቅርበዋል።   በሦስተኛ ደረጃ የአፍሪካ አገሮች ከወርቅ ጀምሮ እስከ ኮባልትና ሊቲየም ድረስ ያላቸውን የተለያዩ የማዕድን ሀብቶች መጠቀም እንዳለባቸው ጠቅሰው፤ በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ ታንታለም የተባለውን ማዕድን በማምረት በዓለም ስድስተኛ ደረጃ መያዟን ገልጸዋል። የአፍሪካ አገሮች ለዘላቂና ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ እድገት የመሰረተ ልማት ግንባታና የዲጂታል መሰረተ ልማት ማስፋፋት ላይ ትኩረት አድርገው መስራት እንዳለባቸው ጠቅሰው፤ ከዚህ አኳያ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚሰራውን ሥራ ለአብነት ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋነኛ የትስስር ማዕከልነቷን ለማፅናት የሚያስችላትን የቢሾፍቱ አየር መንገድ በ12 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር እየገነባች መሆኑን አስረድተዋል። በሌላ በኩል ሦስት ነጥብ አራት ትሪሊዮን ዶላር የሚጠጋ የአገራት አጠቃላይ አገራዊ ምርት የገበያ አቅም ያለው የአፍሪካ ነጸ የንግድ ቀጣና የመሰሉ ፕሮጀክቶች ሊጠናከሩ እንደሚገባ ተናግረዋል። በአምስተኛ ደረጃ የአፍሪካ አገራት ያላቸውን የሰው ኃይል በአግባቡ ሊጠቀሙ እንደሚገባ አስገንዘበው፤ ኢትዮጵያ በተለይም በዲጂታል ቴክኖሎጂው ክህሎት ወጣቶች ያላቸውን አቅም ለማጎልበት የኮደር ሥልጠና እየሰጠች መሆኑን ጠቅሰዋል። ለዚህ ኢኒሼቲቭ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ድጋፍ ማድረጉን ጠቅሰው፤ ለዚህም ምስጋና አቅርበዋል። የተለያዩ የአገራት መሪዎች፣ የኢንቨስትመንት ኩባንያዎች ሥራ አስፈጻሚዎች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና የምርምር ተቋማት ተወካዮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት ዛሬ በዱባይ የተጀመረው ዓመታዊው ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ጉባኤ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ መክሮ ከነገ በስትያ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ለበዓሉ የምርት አቅርቦትን በማሳደግ ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪን ለመከላከል ትኩረት ተሰጥቷል
Sep 7, 2026 94
ሆሳዕና፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ):-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ለዘመን መለወጫ በዓል የምርት አቅርቦትን በማሳደግ ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪን ለመከላከል ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ሀላፊ ባዩሽ ተስፋዬ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት በመጪው የዘመን መለወጫ በዓል ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር የምርት አቅርቦት እንዲያድግ ተደርጓል። ለዚህም መሰረታዊ የፍጆታ ምርቶች አቅርቦትን በማሳደግ ህብረተሰቡ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲሸምት ከማድረግ ባለፈ ህገ ወጥ ተግባራትን የሚቆጣጠር ግብረ ሀይል ተቋቁሞ ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል። ለእዚህም በክልሉ ከሚገኙ ምርት አቅራቢዎች፣ ዩኒየኖችና የሕብረት ሥራ ማህበራት ጋር በቅንጅት በመስራት በመደበኛና በተዘጋጁ ጊዜያዊ የግብይት ማዕከላት ምርት በበቂ ሁኔታ መቅረቡን ተናግረዋል። በዚህም ማህበረሰቡ ለበዓሉ የሚፈልጋቸውን የፍጆታ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ መግዛት እንዲችል ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። ቢሮው ለዘመን መለወጫ በዓል ከ395 ሺህ ሊትር በላይ ዘይት እና ከ7 ሺህ ኩንታል በላይ ስኳር በህብረት ሥራ ማህበራት በኩል እንዲቀርብ ማድረጉንም ባዩሽ (ዶ/ር) አክለዋል። ከዚህ በተጨማሪ ለበዓሉ ጤፍ፣ ስንዴና የቁም እንስሳትን በስፋትና በጥራት ለማህበረሰቡ እየቀረበ መሆኑን አስታውቀዋል:: በዓሉን ምክንያት በማድረግ የሚፈጸም ህገ ወጥነትን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ማህበረሰቡ መረጃ በመስጠት አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርግም አስገንዝበዋል።   የሆሳዕና ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ታሪኬ ግርማ በበኩላቸው በሰጡት አስተያየት ቀደም ሲል የበዓል ወቅትን ምክንያት በማድረግ ይስተዋል የነበረው የዋጋ ጭማሪ አስካሁን አለመኖሩን ተናግረዋል። ለዘመን መለወጫ በዓል የሚሆናቸውን ዶሮ፣ ሽንኩርትና ሌሎች አስፈላጊ ግብዓቶችን መሸመታቸውንም ተናግረዋል። በተለይም በምርት አቅርቦቱ ላይ የተሻለ ሥራ በመሰራቱ አማርጠው ለመግዛት ምቹ ሁኔታ እንደተፈጠረላቸውም ገልጸዋል።   ሌላኛው የከተማው ነዋሪ አቶ ኢዮሲያስ ቀጭኔ በበኩላቸው ለመጪው የዘመን መለወጫ በዓል የሚሆን በሬ ለመግዛት ወደገበያው መምጣታቸውን ተናግረዋል። በገበያው በሬን ጨምሮ የቁም እንስሳት በስፋት መቅረባቸውን ገልጸው፣ በአቅማቸውና በተመጣጣኝ ዋጋ የእርድ በሬ መግዛታቸውን ተናግረዋል።  
በጋምቤላ ክልል የልማት አቅሞችን ወደ ውጤት በመቀየር ዘላቂ እድገት ለማስመዝገብ የተጀመረው ጥረት ይጠናከራል
Sep 7, 2026 153
ጋምቤላ ፤ጳጉሜን 2 /2018 (ኢዜአ)፡-በጋምቤላ ክልል የመልማት አቅሞችን ወደ ውጤት በመቀየር ዘላቂ እድገት ለማስመዝገብ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) ገለጹ። ጳጉሜ 2 የማንሰራራት ቀን ’’ዘላቂ ልማት ለሀገራዊ ማንሰራራት’’ በሚል መሪ ሃሳብ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተከብሯል።   የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት የክልሉን የተፈጥሮ ሀብቶችና የሰው ሀይልን በማቀናጀት ዘላቂ እድገት ለማስመዝገብ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል። በክልሉ የተከናወኑ የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት፣ የቱሪዝም፣ የግብርና እና ሌሎች መስኮች የህዝቡን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ ባለፈ በሀገራዊ ማንሰራራት ውስጥ ድርሻ አላቸው ብለዋል። በቀጣይም እንደ ክልልም ሆነ እንደ ሀገር ያሉትን የመልማት አቅሞች በመጠቀም የተጀመረውን የብልጽግና ጉዞና የኢትዮጵያን ከፍታ እውን ለማድረግ ይበልጥ የምንተጋበት ጊዜ ነው ብለዋል።   በተለይም በክልሉ ያሉትን ሰፊ የተፈጥሮ ሀብቶችና የመልማት እድሎችን በመጠቀም የክልሉን ልማትና እድገት ለማፋጠን ከመቸውም ጊዜ በበለጠ በትኩረት እንደሚሰራ አስገንዝበዋል። የክልሉ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ማክበዲ ኡቻን በበኩላቸው እንዳሉት ዛሬ የምናስበው የኢትዮጵያ የማንሰራራት ቀን የገጠሙንን ፈተናዎች በጽናት ተቋቁመን፤ በህብረትና በጋራ ጥረት ወደ ላቀ ከፍታ የተሻገርንበት ምዕራፍ ነው ብለዋል።   በክልሉ ያሉትን ጸጋዎች በማልማት የህዝቡን ህይወት ለመለወጥ ይበልጥ ጠንክረን እንሰራለን ሲሉም ተናግረዋል። በጋምቤላ ከተማ አደባባይ በተከበረው የጳጉሜ 2 የማንሰራራት ቀን ላይ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችን ጨምሮ የከተማው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም