ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ለአርሶ አደሮች የገበያ ትስስር የመፍጠር ስራ ተጠናክሮ መቀጠል ይገባዋል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 1, 2026 24
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦ አርሶ አደሮች ያመረቱትን ምርት በጥራት ለገበያ ማቅረብ እንዲችሉ የተጀመረው የገበያ ትስስር ስራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ስር የሚተዳደረው የላሜ ዴይሪ ያስገነባውን የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ከንቲባዋ በመልዕክታቸው፤ ፋብሪካው የግሉ ዘርፍ በአግሮ-ኢንዱስትሪው ያለውን ተሳትፎ የሚያሳድግ መሆኑን ገልጸዋል። ጥራቱን የጠበቀ የወተት ምርትን በዓይነትና በብዛት ለከተማዋና ለሀገሪቱ ተጠቃሚዎች በስፋት በማቅረብ፣ የነባሩን የላሜ ዴይሪ ተደራሽነት እንደሚያሰፋም አመልክተዋል። በርካታ የቀንድ ከብት ቢኖርም በእሴት ሰንሰለት እና በምርታማነት ውስንነት ምክንያት የወተት አቅርቦቱ ላይ አሁንም እጥረት እንዳለ ተናግረዋል። ዛሬ በላሜ ዴይሪ የታየው ዘመናዊ በሆነ ሂደት የወተት ምርትን በብዛትና በጥራት እንዲሁም ጤናማና ያለ ማቀዝቀዣ ከ6 ወራት በላይ ሊቆይ በሚችል መልኩ ለገበያ የሚያቀርብ በመሆኑ በዘርፉ የሚታየውን የአቅርቦት ችግር በእጅጉ ያቃልላል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪም፤ አርሶ አደሮች ያመረቱትን ምርት በጥራት ለገበያ ማቅረብ እንዲችሉ የተጀመረው የገበያ ትስስር የመፍጠር ስራ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ከንቲባዋ አሳስበዋል።
የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 1, 2026 38
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018(ኢዜአ)፦ ሁሉን አቀፍ ብልፅግናን በማሳካት የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ስር የሚተዳደረው የላሜ ዴይሪ ያስገነባውን የወተት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት፤ በሀገራችን ከፍተኛ የእንስሳት ሀብት ቢኖርም፥ በወተት ምርትና ምርታማነት እንዲሁም አቅርቦት ላይ ውስንነቶች መኖራቸውን ጠቅሰዋል። ይህ ደግሞ ዜጎች በቂ የወተት ምርት እንዳያገኙ በማድረግ በስርዓተ ምግብ ላይ የራሱ አሉታዊ ተጽዕኖ እንዳለው በመገንዘብ መንግሥት ለዘላቂ መፍትሔ ትኩረት መስጠቱን ገልጸዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት ትውልዱ የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝና ጤናማና አምራች እንዲሆን የወተት ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ተግባራትን ማከናወኑን ተናግረዋል። ላሜ ዴይሪ ባለፉት ጊዜያት በወተትና በወተት ተዋጽኦ አቅርቦት ላይ የራሱን አወንታዊ አስተዋጽኦ ሲያበረክት መቆየቱንም ጠቁመዋል። በዛሬው እለት የተመረቀው ፋብሪካ የድርጅቱን የወተት ማምረት አቅም በተደራሽነትና በጥራት እንደሚያሳድገው ተናግረዋል። ሁሉን አቀፍ ብልፅግናን በአጭር ጊዜ ውስጥ እውን በማድረግ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑንም ነው የገለጹት። በቀጣይም መሰል ስራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ጠቁመው፤ ከተማ አስተዳደሩ ዘርፉን ለመደገፍ ከመቼውም ጊዜ በላይ ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጠዋል። የሜድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፤ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተሟላለት ይህ ፋብሪካ የድርጅቱን የአገልግሎት ጥራት እንደሚያሳድግ ጠቅሰዋል። ፋብሪካው የወተት ተዋጽኦን ያለምንም ማቀዝቀዣ ለስድስት ወራት ማቆየት የሚያስችል መሆኑንም ገልጸዋል። በምረቃ መርኃ-ግብሩ ለወተት አምራቾች፣ አቅራቢዎችና ሌሎች በዘርፉ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት እውቅና ተበርክቷል፡፡
በኢንዱስትሪ ፓርኮች የሀገር ውስጥ ባለሀብቶች ተሳትፎ እያደገ ነው
May 1, 2026 52
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018(ኢዜአ)፦ በኢንዱስትሪ ፓርኮች የሀገር ውስጥ ባለሀብቶች ተሳትፎ ከፍትኛ ዕድገት እያሳየ መሆኑን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍጹም ከተማ ገለጹ። ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚው ይህን ያሉት በቦሌ ለሚ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን የ‎ጵንኤል ኢንዱስትሪ ቆርኪ ፋብሪካ ማስፋፊያ ተመርቆ ሥራ በጀመረበት መርኃ ግብር ላይ ነው። ቀደም ሲል የኢንዱስትሪ ፓርኮች በዋናነት ለውጭ ኢንቨስተሮችና ለውጭ ገበያ ብቻ ታስበው የተገነቡ ቢሆንም አሁን ግን የሀገር ውስጥ ባለሀብቱ የኢንዱስትሪው መሠረት እንዲሆን አዲስ የፖሊሲ ማሻሻያ መደረጉን ተናግረዋል። በተደረገው የፖሊሲ ለውጥና ማበረታቻ ምክንያት በአሁኑ ወቅት በፓርኮች ውሰጥ የሚገኙ የሀገር ውስጥ ባለሀብቶችን ተሳትፎ ከፍተኛ ዕድገት እያሳየ መሆኑን አስታውቀዋል። ጵንኤል ኢንዱስትሪ በቆርኪ ምርትና በብረታብረት የጀመረው የማስፋፊያ ሥራ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል። ኮርፖሬሽኑ ጵንኤል ኢንዱስትሪ ላሳየው ውጤት አስፈላጊውን ድጋፍ ሲያደርግ መቆየቱን ጠቅሰው፥ በቀጣይም አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በኢንዱስትሪ ዘርፍ ለመሰማራት ለሚፈልጉ ሌሎች የሀገር ውስጥ ባለሀብቶች መንግሥት አስፈላጊውን መሠረተ ልማትና ድጋፍ ለማቅረብ ዝግጁ መሆኑንም ገልጸዋል። ‎የጵንኤል ኢንዱስትሪ ዋና ስራ አስኪያጅ ብርቱካን አበበ በበኩላቸው፥ ኢንዱስትሪው ባከናወናቸው ተከታታይ የማስፋፊያ ሥራዎች የቆርኪ ማምረት አቅሙን ወደ 4 ቢሊየን ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል። ቀጣይ የሀገር ውስጥ የቆርኪ ፍላጎትን መቶ በመቶ ለማሟላት እንዲሁም ለጎረቤት ሀገራት በመላክ የውጭ ምንዛሬን ለማስገኘት በትጋት እንደሚሠራ ጠቅሰዋል። ‎ዛሬ የተመረቀው ማስፋፊያ ዘመናዊ የብረታብረት ህትመት (Metal Package Printing) ቴክኖሎጂ ቀደም ሲል ታትመው ከውጭ ይገቡ የነበሩ (Metal Sheets) በሀገር ውስጥ እንዲመረቱ ያስችላል ብለዋል። መንግስት ለፋብሪካው የተለያዩ ማበረታቻዎችን ሲያደርግ እንደነበር አንስተው፤ በቀጣይም ድጋፉ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
በክልሉ በዘጠኝ ወራት ከ57 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል 
May 1, 2026 54
ሚዛን አማን፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ57 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ ዐቢይ አንደሞ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት የክልሉ መንግሥት የአካባቢውን ጸጋዎች በመጠቀም ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ እያደረገ ነው። በዚህም በበጀት ዓመቱ 52ሺህ ሥራ አጥ ዜጎችን ወደ ሥራ ለማሰማራት ታቅዶ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ ከ57 ሺህ ለሚበልጡ ሰዎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ከዕቅድ በላይ ለማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል። በሥራ አጥ ልየታና በስምሪት ሥራ ላይ ባለድርሻ አካላት በኃላፊነት ስሜት መንቀሳቀሳቸው በአፈጻጸሙ ከፍተኛ ውጤት እንዲመዘገብ ማድረጉንም ተናግረዋል። እንደ ዐቢይ (ዶ/ር) ገለጻ ለተደራጁ ወጣቶች ከ658 ሚሊዮን ብር በላይ የገንዘብ ብድር የማሰራጨት፣ የመሥሪያና መሸጫ ቦታ የማመቻቸት እንዲሁም የእርሻ ማሳ የማስተላለፍ ሥራዎች በተሻለ ሁኔታ ተከናውኗል። ከዚህ ባሻገር 15 የእርሻ ትራክተሮች እና 12 የጡብ ማምረቻ ማሽኖች በክልሉ መንግሥት ተገዝተው ለወጣቶች መቅረባቸውን አክለዋል። የሥራ ዕድል ፈጠራው ክህሎት መር እንዲሆን ሥልጠና በማዘጋጀት የወጣቶችን አቅም የማሳደግ ሥራ በቢሮው በኩል መከናወኑንም ገልጸዋል። እንደ ኃላፊው ገለጻ በግብርናና በማኑፋክቸሪንግ ዘርፎች ያለውን ሰፊ አቅም ከሥራ ዕድል ፈጠራ ጋር በማስተሳሰር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ማሳደግ የክልሉ መንግሥት ትኩረት ነው። በክልሉ ሚዛን አማን ከተማ ተደራጅተው የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ወጣቶች መካከል የ"ይቻላል የእንጨትና ብረታ ብረት ሥራ ማኅበር" ሰብሳቢ ዳንኤል ገዛኸኝ ከኮሌጅ ተመርቆ እንደ ወጣ በማህበር ተደራጅቶ ሥራ መጀመሩን ተናግሯል። መንግስት የመሥሪያ ቦታ በመስጠትና የገንዘብ ብድር በማመቻቸት ድጋፍ እንዳደረገላቸው ገልጾ፣ በማኅበሩ ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል መፈጠራቸውን ተናግሯል። የማህበሩ አባላት በዚህ ሥራ ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን እያስተዳደሩ መሆናቸውን ጠቁሞ፣ በቀጣይ ሥራውን ወደ መካከለኛ ኢንዱስትሪ የማሳደግ ራዕይ መሰነቃቸውንም አመልክቷል። በዶሮ ጫጩት እርባታ ሥራ የተሰማሩት ወጣት ቅድስት መኳንንት እና አቤነዘር ዳዊት ከመንግሥት የ250 ሺህ ብር የሥራ ማስጀመሪያ ብድር ወስደው ሥራ መጀመራቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት ከ1ሺህ በላይ የዶሮ ጫጩቶችን በመንከባከብ ላይ መሆናቸውን ገልጸው፣ በቀጣይ የእንቁላል ጣይ ዶሮዎችን በማርባት ሥራችውን ለማስፋፋት ማቀዳቸውንም ተናግረዋል።
ሀገራዊ የሪፎርም ተግባራት ለሠራተኞች ምቹ ምህዳርን በመፍጠር የኢንዱስትሪ ምርታማነትን እያጎለበቱ ነው
May 1, 2026 67
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦ሀገራዊ የሪፎርም ተግባራት ለሠራተኞች ምቹ ምህዳርን በመፍጠር የኢንዱስትሪ ምርታማነትን እያጎለበቱ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ዳንኤል ተሬሳ ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ሠራተኞችና አሠሪዎች ማህበራት ኮንፌዴሬሽኖች ጋር በመተባበር ዓለም አቀፍ የሠራተኞች ቀንን "የሠራተኛው መብት መከበር ለኢንዱስትሪ ሠላም እና ለምርታማነት’’ በሚል መሪ ሀሳብ እያከበረ ይገኛል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ዳንኤል ተሬሳ፤ የሀገርን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ በሥራና ክህሎት ዘርፍ ሰፋፊ የሪፎርም ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ሚኒስትር ዴኤታው በተለይም የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ የክህሎት ማሳደጊያና ለሠራተኞች ምቹ የሥራ ከባቢ መፍጠር የሪፎርሙ ቀዳሚ ትኩረት መሆናቸውን ጠቅሰዋል። መንግሥት እያከናወናቸው ያሉ የሪፎርም ሥራዎች ከአሠሪና ሠራተኛ ምህዳር ጋር እንዲጣጣሙ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የሠራተኛውን የሥራ ሁኔታ ከማሻሻል ባለፈ፣ የሥራ ላይ ደህንነትና ጤንነት ጥበቃ መስፈርቶችን በማዘመን ረገድ ተስፋ ሰጪ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙም እንዲሁ። የሥራ ገበያ ተቋማትን ይበልጥ ውጤታማና ዘመናዊ ለማድረግ የተጀመረው ጥረትም ውጤታማ ነው ብለዋል። እነዚህን እቅዶች በስኬት ለማጠናቀቅና የምርታማነት ግብን ለመምታት የሁሉም ባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ድጋፍና የጋራ ርብርብ ወሳኝ መሆኑን አቶ ዳንኤል ተሬሳ ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ ሠራተኞች ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ በበኩላቸው፤ የሠራተኞች መብት መከበር ለዘላቂ የኢንዱስትሪ ሰላምና ለምርታማነት ዕድገት ወሳኝ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። ኮንፌዴሬሽንኑ ሠራተኞች ተደራጅተው መብትና ጥቅማጥቅሞቻቸው ተጠብቀው ለዘላቂ ሀገራዊ ዕድገት ሚናቸውን እንዲወጡ እየሰራ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንት ዮሐንስ በንቲ (ዶ/ር)፥ መምህራን በእውቀት፣ በክህሎትና በአመለካከት የጎለበቱ ዜጎችን በማፍራት የማይተካ ሚና እንዳላቸው አንስተዋል። የመምህራን መብትና ጥቅሞች እንዲከበሩና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመፍታት ምቹ የሥራ ከባቢ እንዲፈጠርላቸዉ ማህበሩ በስፋት እየሠራ እንደሆነም ነው የጠቀሱት። ለሀገሪቱ ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና ሁለንተናዊ እድገት ማህበሩ ሚናውን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ለግብርና ሜካናይዜሽን ትኩረት ተሰጥቷል
May 1, 2026 65
ነቀምቴ፣ ጥቅምት 23/2018 (ኢዜአ) በምስራቅ ወለጋ ዞን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ለግብርና ሜካናይዜሽን ትኩረት መሰጠቱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ደረጄ ነጋሳ እንደገለጹት፣ በዞኑ የግብርናውን ስራ ውጤታማ ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ ነው። በዞኑ በተለይም የሰብል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግም ለግብርና ሜካናይዜሽን ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል ። ከዚሁ ጎን ለጎን በቴክኖሎጂ የግብአት አጠቃቀም ትኩረት መሰጠቱን ጠቁመው በአጠቃላይ በትራክተር አቅርቦት፣ በምርጥ ዘር፣ በማዳበሪያ እንዲሁም በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅት ላይ ሰፊ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል። የግብርና ቴክኖሎጂ አቅርቦቱ የአርሶ አደሩን ምርታማነት ከማሳደግ ባለፈ ጊዜን፣ ጉልበቱና ገንዘቡን መቆጠብ እንዳስቻለም አክለዋል። ተግባሩን በማስቀጠል በ2018/19 ምርት ዘመን መኽር ወቅት 801 ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ያነሱት ሀላፊው በእስካሁኑም 333 ሺህ ሄክታር መሬት መታረሱን አንስተዋል። በምርት ዘመኑ ከሚለማው መሬትም 225 ሺህ ሄክታሩ በሜካናይዜሽን እንደሚለማ ጠቁመው ለዚህም ቀድሞ ስራ ላይ ካሉት በተጨማሪ 55 ትራክተሮች ለአርሶ አደሩ መቅረባቸውን ጠቁመዋል። በምርት ወቅቱ በተለያዩ ሰብሎች ከሚለማው መሬት 24 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ አመላክተዋል። የዞኑ አርሶ አደሮች በበኩላቸው የግብርና ሜካናይዜሽንን በመጠቀምና ኩታ ገጠም አስተራረስን በመተግበር ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡ አርሶ አደሮች መካከል ማቴዎስ አረጋና አያና ጎበና እንዳሉት፤ ባለፉት አመታት የግብርና ስራቸውን ለማሳካት በኩታ ገጠም መሬታቸውን አልምተዋል። ይህም በባህላዊ መንገድ ከሚያገኙት ምርት በእጥፍ የጨመረ በመሆኑ በዘንድሮው አመትም በጋራ መሬታቸውን በትራክተር እያረሱ መሆኑን ተናግረዋል። ስራውን ይበልጥ ለማሳደግም ተደራጅተው መንግስት ባመቻቸላቸው ብድር ትራክተር መግዛታቸውን ጠቁመዋል። ዘመናዊ እርሻው የምርት ብክነትን ለመቀነስና በሰው ጉልበት በመስራት የሚባክን ጊዜን ለመቀነስ እንዳስቻላቸው የገለጹት ደግሞ አርሶ አደር ተስፋ ስንሻው ናቸው። በአሁኑ ወቅት ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመደራጀት በተመቻቸላቸው የብድር አገልግሎት ትራክተር በመግዛት መሬታቸውን እያረሱ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
በክልሉ ተግባራዊ የተደረገው በቴክኖሎጂ የተደገፈ የግብር አሰባሰብ ሥርዓት ጊዜና ጉልበትን ቆጥቧል        
May 1, 2026 64
ወልቂጤ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ተግባራዊ የተደረገው በቴክኖሎጂ የተደገፈ የግብር አሰባሰብ ሥርአት ጊዜና ጉልበታቸውን እንደቆጠበላቸው ግብር ከፋዮች ገለጹ። የክልሉ ገቢዎች ቢሮ በበኩሉ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ18 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን አስታውቋል፡፡ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ገቢዎች ቢሮ የዘረጋው በቴክኖሎጂ የተደገፈ የግብር ክፍያ ሥርአት ግልጸኝነትና ብልሹ አሰራርን በማስቀረት ጊዜና ገንዘባቸውን መቆጠብ እንዳስቻላቸው በክልሉ የሚገኙ ነጋዴዎች ለኢዜአ ገልጸዋል። በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል በወልቂጤ ከተማ በንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩት አቶ ባይከዳኝ ገብሩ እና አቶ አብድልሃሚድ አብድልካፍ እንዳሉት ግብራቸውን በወቅቱ በመክፈል የዜግነት ግዴታቸውን ተወጥተዋል። ቢሮው የዘረጋው በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብር አሰባሰብ ሥርአት ነጋዴው ግብሩን በፍትሃዊነት፣ በግልጽነትና ከብልሹ አሰራር በጸዳ መልኩ መክፈል እንዲችል ዕድል መስጠቱንም ጠቁመዋል። ዘመናዊ አሰራሩ ግብራቸውን ባሉበት ቦታ ሆነው ሥራቸውን እያከናወኑ መክፈል እንዳስቻላቸው ገልጸው፣ ይህም ጊዜና ጉልበታቸውን ለመቆጠብ እንዳገዛቸው አመልክተዋል። ግብር መክፈል ለሁለንተናዊ ልማትና እድገት ወሳኝ በመሆኑ በየዓመቱ የሚጠበቅባቸውን ግብር በታማኝነት መክፈላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል። በተሰማሩበት የሆቴል ሥራ የሚጠበቅባቸውን ግብር በወቅቱ በመክፈል ለሀገር ልማት የበኩላቸውን እየተወጡ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በክልሉ የቡታጀራ ከተማ ነዋሪው አቶ ኑሩ ደድገባ ናቸው። የግብር አሰባሰብ ሥርዓቱ በቴሌ ብርና በሌሎች ቴክኖሎጂዎች መደገፉ እንግልትን በማስቀረት ጊዜያቸውን ለመቆጠብ እንዳስቻላቸው አክለዋል፡፡ የሚሰበሰበው ገቢ በከተማዋ የህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚነት እያረጋገጠ መሆኑን በተጨባጭ በማየታቸው ግብራቸውን በታማኝነት ለመክፈል እንዳነሳሳቸው ገልጸዋል። የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ይድረሱ ተስፋዬ የገቢ አሰባሰብ ሥርዓቱ በቴክኖሎጂ መታገዙ ብልሹ አሰራሮችን ለማስቀረት አግዟል ብለዋል። በዚህም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከቀጥታ ታክስ፣ ቀጥታ ካልሆኑና ከሌሎች የገቢ አርዕስቶች ከ810 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን ገልጸዋል። ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከ299 ሚሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለውም አመልክተዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ቀመሪያ ረሻድ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የገቢ አሰባሰቡን በማዘመንና የገቢ አማራጮችን በማስፋት ልማትን ለማፋጠን እየተሰራ ነው። የገቢ አሰባሰቡ በቴክኖሎጂ እንዲደገፍ መደረጉ የደንበኞችን እርካታ ለማሳደግ የራሱን አስተዋጽኦ ማድረጉን ጠቅሰው፣ የገቢ ሕጉን ባላከበሩ አካላት ላይም እርምጃ መወሰዱን አስረድተዋል። ለአብነትም ባለፉት ዘጠኝ ወራት የስነ ምግባር ጥሰት በፈጸሙ 72 ባለሙያዎች እና የገቢ ሕጉን ባላከበሩ ከ700 በላይ ግብር ከፋዮች ላይ ህጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ ተወስዷል ብለዋል፡፡ የገቢ አሰባሰቡን በማዘመን በበጀት ዓመቱ ለመሰብሰብ ከታቀደው 27 ቢሊዮን ብር ገቢ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 18 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ መቻሉን ጠቁመዋል። ገቢው ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ7 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለውም ተናግረዋል።
በክልሉ የቡና ልማትን በማጠናከር የዘርፉን ገቢ ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
May 1, 2026 65
ሀላባ ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የቡና ልማትን በማጠናከር የዘርፉን ገቢ ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ፡፡ ክልላዊ የበልግ ወቅት የቡና ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በሀላባ ዞን ዌራ ወረዳ አለምጤና ቀበሌ ተካሂዷል፡፡   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የግብርናና ገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡስማን ስሩር እንዳሉት በክልሉ የቡና ሽፋንን ለማሳደግ በቤተሰብ ደረጃ ሊተገበር የሚችል ኢንሼቲቭ ተቀርፆ ወደ ተግባር ተገብቷል፡፡ በዚህም ጥራት ያለውና ምርታማ የቡና ችግኞችን በማልማት የቡናን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። ለተግባራዊነቱም 44 ነጥብ 6 ሚሊዮን የቡና ችግኝ ለመትከል ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን የገለጹት ሃላፊው፣ ይህም የክልሉን የቡና ሽፋን ወደ 180 ሺህ ሄክታር ያሳድገዋል ብለዋል። የክልሉ ቡናና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ቶፊቅ ጁሃር በበኩላቸው፣ በክልሉ ኩታ ገጠም የቡና ልማት ሥራ በማከናወን በልማቱ ተጨባጭ ውጤት ለማምጣት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው ብለዋል።   ባለፉት ዓመታት በክልሉ 169 ሺህ ሄክታር ማሳ ቡና በማልማት ምርቱ ለማዕከላዊ ገበያ እየቀረበ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በዞኑ ከዚህ ቀደም ባልተለመደ መልኩ ቡናን በኩታ ገጠም በማልማት ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል ያሉት ደግሞ የሀላባ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሙህዲን ሁሴን ናቸው። ቀደም ሲል የዞኑ የቡና ሽፋን ዝቅተኛ እንደነበር አንስተው ባለፉት ሁለት ዓመታት ለዘርፉ በተሰጠው ትኩረት 298 ሄክታር ማሳ በቡና ማልማት ተችሏል ብለዋል።   ቡናን ማልማት ከጀመሩ ወዲህ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ስለመምጣቱ የተናገሩት ደግሞ በተከላ መርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉት በሃላባ ዞን ዌራ ወረዳ ዓለም ጤና ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር ኢመም ሰልማን ሰላቶ ናቸው፡፡ የቡና ልማቱን ከሌላ የግብርና ሥራቸው ጋር አጣምረው በማከናወን ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡ በቡና ችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ላይ የክልሉና የዞን ከፍተኛ አመራሮች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል፡፡
በዞኑ የእንሰት ልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እያገዘ ነው
May 1, 2026 69
ዲላ ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦በጌዴኦ ዞን እንሰትን በስፋት በማልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በተሰጠው ልዩ ትኩረት አበረታች ውጤት እየተገኘ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለጸ። በዞኑ በተያዘው ዓመት 57 ሚሊዮን በላይ የእንሰት ችግኝ ተከላ መከናወኑ ተመላክቷል። የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ ተገኝ ታደሰ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ከ35 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በእንሰት ተክል ተሸፍኗል።   ዘንድሮም ልማቱን ለማስፋፋት ባለፋት ሁለት ወራት ከ57 ሚሊዮን በላይ የእንሰት ችግኞች ተከላ መከናወኑን ተናግረዋል። ከተክሉ የሚገኝ ዓመታዊ የምርት መጠንም ከነበረበት 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ወደ 2 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል ማደጉን አመልክተዋል። ይህም ከተረጅነት በመላቀቅ በምግብ ራስን ለመቻል የሚደረገውን ጥረት ከማጠናከር ባለፈ ዞኑ የሚታወቅበትን የጥምር ግብርና ባህልን ለማዳበር የሚያስችል ነው ብለዋል። ልማቱን ለማስፋፋትና ለማዘመን የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። የይርጋጨፌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዳዊት ቡኔ በወረዳው ቡናና እንሰትን በዘመናዊ መንገድ በስብጥር በማልማት የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የይርጋጨፌ ቡና ተፈጥሯዊ ጣዕሙ ተጠብቆ እንዲቆይ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል።   ዘንድሮ የበልጉን ዝናብ በመጠቀም በ155 ሄክታር መሬት ላይ በኩታ ገጠም ቡናና እንሰት በስብጥር መተከሉን አንስተው ይህም ዘመናዊ አሰራርን በማጠናከር ምርታማነትን የሚያሳድግ መሆኑን ጠቁመዋል። የይርጋጨፌ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሃይሌ ቦራ በበኩላቸው ባለፉት አመታት ከመንግስት ያገኙትን የእንሰት ችግኝ በዘመናዊ አሰራር በመስመር በማልማት በሁለት አመት ጊዜ ውስጥ ለምርት መድረሱን ተናግረዋል።   በአሁኑ ወቅት የቆጮ ምርት ከቤተሰብ ፍጆታ አልፎ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አንስተዋል። እንሰት በኩታ ገጠም በዘመናዊ መንገድ ከቡና ጋር በስብጥር ማልማታቸው ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ያነሱት ደግሞ በወናጎ ወረዳ የቱማታ ጭራቻ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ብርሃኑ ማሞ ናቸው።
በዞኑ በዘጠኝ ወራት ከ41 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች የሀይል አማራጭ ተጠቃሚ ሆነዋል
May 1, 2026 65
ደሴ ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ወሎ ዞን ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ41 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በተለያዩ የሀይል አማራጮች ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የዞኑ ውሃና ኢነርጂ ልማት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ጌታቸው ጽጌ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በዞኑ የገጠሩን ማህበረሰብ በአማራጭ ሀይል ተጠቃሚ በማድረግ አኗኗሩን ለማዘመን በትኩረት እየተሰራ ነው። በበጀት ዓመቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራትም የታዳሽ ሀይል ቴክኖሎጂን በማስፋፋት ከ41ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን የአማራጭ ሀይል ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። ለዚህም ከ33 ሺህ 800 በላይ የተሻሻሉ ማገዶ ቆጣቢ ምድጃዎችን የማሰራጨት፣ 6ሺህ 947 በፀሐይ ሃይል የሚሰሩ ሶላር ፓኔሎችን የማቅረብ እንዲሁም 311 ባዮጋዝ ቴክኖሎጂ የመገንባት ሥራ መከናወኑን ገልጸዋል። በቀሪ ወራትም በግንባታ ላይ ያሉ 461 ባዮጋዞችን በማጠናቀቅ ወደ ሥራ ለማስገባት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። አማራጭ ሀይሉ ለምግብ ማብሰያና ለመብራት አገልግሎት ይጨፈጨፍ የነበረን ደን ከማዳን በተጨማሪ በጭስ ምክንያት በሴቶች ላይ ሲከሰት የነበረን የጤና ችግር ማቃለል ተችሏል ብለዋል። አርሶ አደሩ በተመቻቸለት አማራጭ የሃይል አቅርቦት መጠቀሙ ጊዜ፣ ጉልበትና ወጪውን ከመቆጠብ ባለፈ ኑሮውን ለማሻሻልና ለማቅለል እንዳስቻለውም አስረድተዋል። በተለይ የባዮ ጋዝ ተረፈ ምርትን ለአፈር ማዳበሪያነት መጠቀሙ የማዳበሪያ ወጪን ለመቀነስና ምርታማነትን ለማሳደግ አስተዋጽኦው የጎላ መሆኑን ነው የገለጹት። በተሁለደሬ ወረዳ የቀበሌ 08 ነዋሪ አርሶ አደር ያሲን አህመዴ በበኩላቸው፣ የተገነባላቸውን የባዮጋዝ ቴክኖሎጂ ምግብ ለማብሰልና ለመብራት አገልግሎት መጠቀም በመቻላቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። ለማገዶ ፍለጋ ያጠፉት የነበረውን ጊዜ፣ ጉልበትና ወጪ ከመቆጠብ ባለፈ ተረፈ ምርቱን ለማዳበሪያነት በመጠቀም የመሬት ለምነትና ምርታማነታቸውን ማሳደጋቸውን ጠቁመዋል። የወረባቦ ወረዳ ነዋሪ ወይዘሮ ከድጃ ሰይድ በሰጡት አስተያየት፣ የማገዶ ቆጣቢ ምድጃ ተጠቃሚ መሆናቸው ኑሯቸውን ማቃለሉን ተናግረዋል። በተለይ በጭስ አማካኝነት ይፈጠር የነበረውን የጤና ችግር በማስቀረቱ መደሰታቸውን ገልጸዋል። በዞኑ ባለፈው በጀት ዓመት ከ56 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በተለያዩ የሀይል አማራጭ ቴክኖሎጂዎች ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ከዞኑ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
4ኛው የኢትዮጵያ ታምርት ዓለም አቀፍ ኤክስፖ በመጪው እሁድ በይፋ ይከፈታል
May 1, 2026 90
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦4ኛው የኢትዮጵያ ታምርት ዓለም አቀፍ ኤክስፖ እሁድ ሚያዝያ 25 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ በይፋ እንደሚከፈት የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ መላኩ አለበል አስታወቁ። ሚኒስትሩ በሰጡት መግለጫ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኢንዱስትሪዎች ያጋጥማቸው የነበሩ ችግሮች ደረጃ በደረጃ እንዲፈቱና የማምረት አቅማቸው እንዲጎለብት መደረጉን አንስተዋል። 4ኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሀሳብ ከሚያዝያ 25 እስከ 30 /2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ ገልጸው፥ የኢትዮጵያን ምርቶች ማስተዋወቅና ተጨማሪ የገበያ ዕድሎችን ማስፋት የኤክስፖው ዋና ዓላማ ነው ብለዋል። የገበያ ትስስሮችን ለመፍጠርና የምርት ጥራትን ለማሻሻልም ጉልህ ሚና ይኖረዋል ነው ያሉት። ፈጠራን ማበረታታትም አንዱ የኤክስፖው ዓላማ መሆኑን ጠቅሰው፤ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የልምድ ልውውጥ መፍጠርም ዋነኛ ግቡ መሆኑን ተናግረዋል። በኤክስፖው 850 የንግድ ስምምነቶች እንደሚደረጉ ጠቅሰው ከአምስት ቢሊዮን ብር በላይ ግብይት ይፈፀማል ተብሎ እንደሚጠበቅ ጠቁመዋል። በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ለአምስት ቀናት የሚካሄደውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ከ150 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጭ ዜጎች እንደሚጎበኙት በመግለጫው ተብራርቷል። በኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶችን ከማስተዋወቅ ባለፈ የተለያዩ የፓናል ውይይቶች፣ የምርት ልማት ውድድሮች፣ የተሻለ አፈፃፀም ላላቸው ኢንዱስትሪዎች የዕውቅና ፕሮግራም እና ሌሎችም መርሃ-ግብሮች እንደሚከናወኑ በመግለጫው ተመላክቷል።
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የቱሪዝም መዳረሻዎችን የማልማት ስራ እየተከናወነ ነው
May 1, 2026 68
ጭሮ ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸውን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ባህልና ቱሪዝም ፅህፈት ቤት አስታወቀ። በፅህፈት ቤቱ የቱሪዝም መዳረሻዎች ቡድን መሪ አቶ ሳንዮ አደም ለኢዜአ እንደገለፁት ፤ በዞኑ የሚገኙ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በመለየት የማስተዋወቅና የማልማት ስራ እየተካሔደ ነው።   መስህቦቹን ለቱሪዝም ልማቱ ከማዋል በተጨማሪ የአካባቢው ማሕበረሰብን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ በሚያስችል መልኩ እንዲደራጁ እየተደረገ መሆኑን ነው ያመለከቱት። እስካሁንም ከ50 በላይ መስህቦች በቱሪዝም መዳረሻነት ተለይተው በፅሑፍ የተሰነዱ ሲሆን ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆንም ስፍራዎቹን የማስተዋወቅና የማልማት ስራ መጀመሩን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም የኦዳ ቡልቱም አርዳ ጅላ እና የጨርጨር ሀይቅን ጨምሮ ጥንታዊ ዋሻዎች ያሉበትን አካባቢ ምቹ የማድረግ ስራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ካሉ አስራ አንድ የኢኮ ቱሪዝም መዳረሻዎች አንዱ የሆነው የጨርጨር ሀይቅ የውሀ መጠኑ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱን ገልፀው ለቱሪዝም መዳረሻነት ለማገልገል እንዲችል እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። በገዳ ስርዓት ከሚታወቁት አምስት ኦዳዎች አንዱ የሆነውን የኦዳ ቡልቱም አካባቢን ከዚሁ ሀይቅ ጋር በመሰረተ ልማት በማገናኘት የአገር ውስጥና የውጭ ጎብኚ ለመሳብ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልፀዋል።   የቦኬ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ መሀመድዘይን ጀማል እንዳሉት በወረዳው ረጅም ዕድሜ ያስቆጠረው ጥንታዊ መስጂድን እና የጨርጨር ሀይቅ ጎብኚዎችን ለመሳብ እንዲውሉ መሰረተ ልማቶች እንዲሟላላቸው እየተደረገ መሆኑን ገልፀዋል። በተያዘው ዓመትም ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ከዋናው መንገድ እስከ ጨርጨር ሀይቅ የሚወስደው መንገድ እየተገነባ መሆኑን አንስተዋል። የአካባቢው ወጣቶች ሐይቁን በመጠበቅና በመንከባከብ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማድረግም የወረዳው አስተዳደር ከ20ሺ በላይ የዓሳ ጫጩት በሀይቁ ውስጥ እያረባ መሆኑን ገልፀዋል።
በአማራ ክልል በመኸር ወቅት ከ336 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት በሩዝ ሰብል ይለማል
May 1, 2026 111
ባህር ዳር፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በተያዘው የመኸር ወቅት ከ336 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት በሩዝ ሰብል እንደሚለማ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማንደፍሮ አስላከ(ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በመኸር የምርት ዘመን በሩዝ ልማት ላይ ለውጥ የማምጣት ግብ ተይዞ ወደ ስራ ተገብቷል። የሩዝ ልማቱን በኩታ ገጠም በማረስ፣ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በወቅቱ ተደራሽ በማድረግ የሚጠበቀውን ምርት መሰብሰብ የሚያስችሉ ተግባራት ከወዲሁ መጀመራቸውን ገልፀዋል። ከ336 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሩዝ በመሸፈን ከ18 ነጥብ አምስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ሩዝን ጨምሮ 10 ስትራቴጂካዊ ሰብሎች በልዩ ሁኔታ በክላስተር ለማልማት አቅጣጫ ተቀምጧል ያሉት አቶ ማንደፍሮ ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ በመፍጠር እቅዱን ለማሳካት ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል። የሩዝ ልማት በደቡብ ጎንደር ፎገራ ወረዳና አካባቢው ብቻ ተወስኖ የነበረ ሲሆን በአሁኑ ወቅት ተስማሚ ስነ ምህዳርና የአየር ንብረት ባላቸው አብዛኛው የክልሉ ዞኖች እየተለመደ መምጣቱን ገልፀዋል። በደቡብ ጎንደር ዞን ፎገራ ወረዳ የቋር ሚካኤል ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር አበራ ዘመናይ እንደገለጹት፣ ሁለት ሄክታር ማሳቸውን በሩዝ ሰብል ለመሸፈን ዝግጅት እያደረጉ ነው። በዘርፉ ምርታማነትን ለማሳደግ የአፈር ማዳበሪያ ቀድመው መውሰዳቸውን ጠቅሰው በሄክታር እስከ 50 ኩንታል ምርት ለማግኘት እንደሚሰሩም አስረድተዋል። ባለፈው የመኸር ምርት ዘመን በክልሉ በሩዝ ከለማው 208 ሺህ 636 ሄክታር መሬት ከ11 ነጥብ አምስት ሚሊየን ኩንታል በላይ ምረት መመረቱን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በከተማዋ የተጀመሩ የለውጥ ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት እያረጋገጡ ነው
May 1, 2026 77
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዝያ 23/2018 (ኢዜአ)፦በወላይታ ሶዶ ከተማ የተጀመሩ የለውጥ ስራዎች የከተማውን ህዝብ ተጠቃሚነት እያረጋገጡ መሆናቸው ተመላከተ። በወላይታ ሶዶ ከተማ ከ69 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ መሰረተ ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) በፕሮጀክቶቹ ምረቃ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት የክልሉ መንግስት የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመፍታት በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   የወላይታ ሶዶ ከተማ የጀመራቸው የለውጥ ስራዎች የከተማውን ህዝብ ተጠቃሚነት እያረጋገጡ መሆናቸውን ጠቅሰው የክልሉ መንግስት ቀጣይነት ያለውን ልማት ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት እንደሚሰራ ተናግረዋል። በከተማ አስተዳደሩ ተገንብተው የተመረቁ ፕሮጀክቶች ብልፅግናን በተጨባጭ ለማረጋገጥ የተደረጉ ጥረቶች ማሳያ መሆናቸውን አክለዋል፡፡ የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማሪያም በበኩላቸው የላሬና ኦሴ እና ጉትቶ ዱቡሻ ቀበሌ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ግንባታ መጠናቀቅ ለህብረተሰቡ የረጅም ጊዜ ጥያቄ ምላሽ የሰጠ መሆኑን ጠቁመዋል።   ፕሮጀክቱ ከ55 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባ ሲሆን ከ36 ሺህ በላይ የሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ተናግረዋል። ከንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቱ ባሻገር ከ5 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባው የድልድይ እና ከ9 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባው የቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት በአጭር ጊዜ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን ገልጸዋል። የህዝቡን ጥያቄ መነሻ በማድረግ በሁሉም ክፍለ ከተሞች የተጀመሩ የመሰረተ ልማት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። የወላይታ ሶዶ ከተማ ውሃና ፍሳሽ ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ሀብታሙ ፋንታ ኮርፖሬሽኑ አቅሙን አሳድጎ የውሃ ተቋማትን በአጭር ጊዜ ውስጥ በጥራት ገንብቶ እያስረከበ መሆኑን ጠቁመዋል።   ፕሮጀክቱ የከተማውን የንጹህ መጠጥ ውሃ ሽፋን ከ85 በመቶ በላይ እንደሚያደርሰው ገልጸው ኮርፖሬሽኑ በቀጣይም የከተማውን ዕድገት በሚመጥን መልኩ የንጹህ መጠጥ ውሃ ተደራሽነትን ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት ይሰራል ብለዋል። በከተማው መርካቶ ክፍለ ከተማ የቦሳ ዚጋ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ባሳ ባራታ እና አቶ ኮርካ ኮሮቶ በአካባቢው የነበረው ድልድይ ተበላሽቶና በጎርፍ ተወስዶ በማህበራዊ ግንኙነታቸው ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ሲያሳድር መቆየቱን ገልጸዋል።   የድልድዩ መገንባት ችግሩን ሙሉ በሙሉ የሚቀርፍ በመሆኑ የከተማ አሰተዳደሩን አመስግነው ዘላቂ አገልግሎት እንዲሰጥ ጥበቃ እንደሚያደርጉለትም ተናግረዋል። የላሬና ኦሴ እና ጉቱቶ ዱቡሻ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ አበራ ጃጎ እና ታሪኩ ላአ በበኩላቸው በአካባቢው የንፁህ መጠጥ ውሃ ባለመኖሩ የወንዝ ውሃ በመጠጣት ለበሽታ ሲጋለጡ መቆየታቸውን አስታውሰዋል።   የከተማ አስተዳደሩ ችግሩን ለመቅረፍ ባደረገው ጥረትና ቁርጠኝነት ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁመው የውሃ ተቋሙ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት እንዲሰጥ እንክብካቤ እንደሚያደርጉም ተናግረዋል።
አዲሱ የአራዳ ፓርክ፦ የታሪክ፣ የውበትና የዘመናዊነት መገናኛ !
Apr 30, 2026 385
የአራዳ ፓርክ የጉስቁልና ታሪክን፣ የቆሻሻና የብክለት ስጋትን እንዲሁም የአስከፊ ድህነትን ገጽታ የቀየርንበት ታላቅ ፕሮጀክት ነው። የባዕዳንን አሉታዊ የታሪክ አሻራዎች በመናድ፣ የኢትዮጵያን ውበትና የትውልድን አዲስ ታሪክ በጋራ በማተም አዲሱን ማንነታችንን ገንብተናል። ከፒያሳ አካባቢ የተነሱ ነዋሪዎቻችንን ለሰው ልጅ ክብር ከማይመጥኑና ከተጎሳቆሉ መኖሪያዎች አውጥተን፤ እጅግ ጤናማ፣ ነፋሻማና ሰብአዊ ክብርን የሚመጥን መሰረተ ልማት የተሟላለት መኖሪያ “ቤት ለእምቦሳ” ብለን አስረክበናል። ማህበራዊ መስተጋብራቸው ሳይቋረጥ እድርና እቁባቸውን ጠብቀው በጋራ እንዲኖሩም አድርገናል። ፒያሳን መልሰን ስንገነባ እውነተኛ ስልጣኔንና አራድነትን በሚያሳይ መልኩ ነው። ወንዞቻችን ከቆሻሻና ከበሽታ አምጪነት ተላቀው ዛሬ የቱሪስት መዳረሻ፣ የተፈጥሮ ውበት መገለጫና የሥራ ዕድል መፍጠሪያ ሆነዋል።   የአራዳ ፓርክ በ40 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ የተቀናጀ የመሰረተ ልማትና የአገልግሎት ማዕከል ሲሆን፣ በውስጡ የሚከተሉትን ዋና ዋና አገልግሎቶች ይዟል፦ 1. የትራንስፖርትና የመንገድ መሰረተ ልማቶች • የአስፓልት መንገድ፦ 5 ኪ.ሜ. የሚረዝም የውስጥ ለውስጥ መንገድ። • የእግረኛ መንገድ፦ 6 ኪ.ሜ. ርዝመት ያለው ምቹ የእግር ጉዞ መስመር። • የብስክሌት መስመር፦ 5 ኪ.ሜ. ርዝመት ያለው የሳይክል ሌን። • የመሮጫ ትራክ፦ 5 ኪ.ሜ. የሚረዝም ለስፖርተኞች የተዘጋጀ መስመር።   2. የንግድና የፋይናንስ አገልግሎቶች • የንግድ ሱቆች፦ ከፒያሳ ለተነሱ ነጋዴዎች ቅድሚያ የተሰጠባቸው 131 ዘመናዊ ሱቆች። • ምግብና መጠጥ፦ 7 ካፌዎችና ሬስቶራንቶች። • ግብይትና ባንክ፦ 1 ትልቅ ሱፐርማርኬት እና 1 የባንክ ቅርንጫፍ። 3. የስፖርት፣ የኪነ-ጥበብና የመዝናኛ መገልገያዎች • ዘመናዊ የስፖርት አሬና፦ አንድ (1) ዘመናዊ የአካል ብቃት ማዕከል (Gym) እና 7 አዳራሾች። • መድረኮች፦ 8 ፕላዛዎችና 3 አንፊ-ቴአትሮች (ለተለያዩ ኩነቶች ማዘጋጃ የሚውሉ)። • ልዩ ውበት፦ በአይነቱ ልዩ የሆነ “ዳንሲንግ ፋውንቴን” (ተንቀሳቃሽ ፏፏቴ)። • ብሔራዊ ምልክት፦ በሀገራችን ረጅሙ የሆነው ባለ 100 ሜትር የብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ መስቀያ። 4. ለሕፃናትና ለቤተሰብ • የሕፃናት መጫወቻ፦ 4 በሚገባ የተሟሉ ዘመናዊ የመጫወቻ ስፍራዎች። • ትንሿ ከተማ፦ ሕፃናት ስለ ሀገራቸው እውቀት የሚቀስሙበትና የሚዝናኑበት ልዩ ስፍራ።   5. የተፈጥሮ ልማትና የንፅህና አገልግሎቶች • አረንጓዴ ልማት፦ 15 ሄክታር መሬት በሳርና በተክሎች የተሸፈነ፣ በፓርኩ ውስጥ በተለያዩ ቦታዎች የሚገኙ 22 የሕዝብ መጸዳጃ ቤቶች። • ፓርኪንግ፦ በአንድ ጊዜ 131 መኪናዎችን መያዝ የሚችል ሰፊ ማቆሚያ ወዘተ አገልግሎቶችን አካትቷል። የአራዳ ፓርክ የመሬት አጠቃቀምን በላቀ ደረጃ ጥቅም ላይ ያዋለ ፕሮጀክት ነው። መሬትን ከስር ለሱቅና ለአዳራሽ፣ ከላይ ደግሞ ለፕላዛ በመጠቀም ውስን የሆነውን የከተማ መሬት በብቃት ተጠቅመናል። በተጨማሪም በአካባቢው የነበሩ ከ700 በላይ ቤቶችና ሕንፃዎች ታሪካዊ ይዘታቸውን ጠብቀው እንዲታደሱ ተደርጓል። ይህ ፓርክ ከንግድ እስከ ስፖርት፣ ከቤተሰብ መዝናኛ እስከ ዓለም አቀፍ የኪነ-ጥበብ መድረኮችን አጣምሮ የያዘ የከተማዋ አዲስ የቱሪስት መዳረሻ ነው። እንኳን ደስ አለን!
‎ኢትዮጵያ በምናብ የምትሳል ህልም ብቻ ሳትሆን በተግባር የምትገነባ እውነታ ናት - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 30, 2026 241
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በምናብ የምትሳል ህልም ብቻ ሳትሆን በተግባር የምትገነባ እውነታ ናት ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት የአራዳ ፓርክ አዲስ አበባን ለመለወጥ ያለውን ርዕይ በተግባር ያሳየ አንዱ ስራ መሆኑን ገልጸዋል።   ቀደም ሲል ተዘንግቶና ለአደጋ ተጋልጦ የነበረው የአራዳ አካባቢ፣ ዛሬ ተመልሶ ተገንብቶ አስደናቂ የከተማ አካል መሆን መቻሉን አስታውቀዋል። ኢትዮጵያ በምናብ የምትሳል ህልም ብቻ ሳትሆን በተግባር የምትገነባ እውነታ መሆኗን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።   ጤናማ፣ ጽኑ፣ ለመጭው ትውልድ ተስፋን ከተጨባጭ ሀብት ጋር የምትሰጥ፣ በአፍሪካ መሪ፣ በዓለም መድረክ ደግሞ ተወዳዳሪ የሆነች ሀገር እየተገነባች እንደሚገኝም ነው የተናገሩት። ይህንን ተስፋ ወደ እውነታ የመለወጥ ተግባር በየቀኑ እንደሚቀጥልም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው አረጋግጠዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አዲሱ አራዳ ፓርክን መርቀው ከፈቱ
Apr 30, 2026 250
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ):- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አዲሱ አራዳ ፓርክን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። የአዲሱ አራዳ ፓርክ ታሪክ ጥልቅ ለውጥ የታየበትና በዛሬው ዕለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ይፋ የተደረገ ታላቅ ፕሮጀክት መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ገልጿል። ቀደም ሲል ተዘንግቶ፣ ለአደጋ የተጋለጡ ቤቶች የነበረው ይህ 40 ሄክታር መሬት፣ ዛሬ ተመልሶ ተገንብቶ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት የሚሰጥ ቀዳሚ የከተማ መዳረሻ መሆኑን አመልክቷል። ይህ ፕሮጀክት ፓርክ ብቻ ሳይሆን፤ የተቀናጀ መሠረተ ልማትና የመሬት አጠቃቀም ብቃት የታየበት ጥበብ መሆኑን አስታውቋል።   ከ700 በላይ ነባር ቤቶችንና ሕንፃዎችን በማደስ፣ ልማቱ ማኅበረሰቡን የሚያገል ሳይሆን የሚያቅፍ እንዲሆን መደረጉንም ጠቁሟል። • ለምለም የከተማ መናፈሻ ከጠቅላላው 40 ሄክታር መሬት ውስጥ 15 ሄክታሩ በአረንጓዴ የተሸፈነ ሲሆን፤ ይህም ለአዲስ አበባ መሀል እንደ መተንፈሻ ሆኖ ያገለግላል። • ከተማን ማገናኘት በዲዛይኑ ውስጥ ለእንቅስቃሴ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቷል፤ ይህም 5 ኪሎ ሜትር የአስፋልት መንገድ፣ 6 ኪሎ ሜትር የእግረኛ መሄጃ፣ እንዲሁም ለብስክሌትና ለሩጫ የሚሆኑ 5 ኪሎ ሜትር መንገዶችን ያካተተ ሲሆን፤ ይህም ጤናማና ንቁ የአኗኗር ዘይቤን ያበረታታል።   • የኢኮኖሚ ጥንካሬ ፓርኩ ለንግድ እንቅስቃሴዎች ትልቅ ማዕከል ነው፤ ከፒያሳ ለተነሱ ነጋዴዎች ቅድሚያ የሚሰጡ 131 የንግድ ሱቆች፣ 7 ካፌዎችና ምግብ ቤቶች፣ ሱፐርማርኬትና የባንክ ቅርንጫፍ በመያዝ የኢኮኖሚ ዘላቂነትን ያረጋግጣል። • ጤናና ባህል ከአረንጓዴው ስፍራ በተጨማሪ ፓርኩ ዘመናዊ የስፖርት ማዘውተሪያ፣ ጂምናዚየም እና 7 አዳራሾችን ይዟል። ከዚህም ጎን ለጎን ለዓለም አቀፍ ደረጃ ጥበባትና ለማኅበራዊ ኩነቶች የተዘጋጁ 8 አደባባዮችና አምፊቲያትሮችን አካቷል። • ቤተሰብና ዘመናዊነት ሕፃናት የሚጫወቱባቸው 4 ስፍራዎችና ልዩ የሆነ 'ትንሿ ከተማ' (Miniature City) ተገንብቶላቸዋል። በፈጠራ የታጀበ ባለብዙ ወለል ዲዛይን በመጠቀም በግርማ ሞገስ በተገነቡ አደባባዮች ሥር ደማቅ የንግድ ስፍራዎችን በማካተት የአራዳ ፓርክ ውድ የሆነውን የከተማ መሬት በእያንዳንዱ ስንዝር በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውል ማድረጉንም አመልክቷል።
በክልሉ የግብርና ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ጥረት በተቀናጀ መልኩ እየተከናወነ ነው
Apr 30, 2026 180
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 22/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በቅንጅት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ገለጸ። የሲዳማ ክልል የእርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ መምሩ ሞኬ፤ በክልሉ የግብርና ልማት እንቅስቃሴንና የተገኙ ውጤቶችን በማስመልከት ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል።   በማብራሪያቸውም በክልሉ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለዚህም ከሰባት በላይ አዳዲስ የግብርና ልማት ኢንሸቲቮች ተቀርጸው በሥራ ላይ በማዋል የምርት አማራጭንና ምርታማነትን የማሳደግና የሥራ ዕድልን የማስፋት ተግባራት እየተከናወኑ ነው ብለዋል። ለመስኖ ልማት በተሰጠው ትኩረት በትናንሽ የውሃ አማራጮች፣ ከ28 በሚበልጡ አነስተኛ፣ መካከለኛና ከፍተኛ የመስኖ አውታሮች ሰፊ መሬት ማልማት መቻሉን ጠቅሰዋል።   ለአብነትም በተያዘው ዓመት ከ100 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሁለት ዙር በማልማት ከ22 ነጥብ 2 ሚሊዮን በላይ ኩንታል ምርት መሰብሰቡን ገልጸዋል። የመስኖ ልማቱ ገበያን ከማረጋጋት ባለፈ ለሥራ ልድል ፈጠራም ጉልህ አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። የመስኖ ልማቱ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ከፍተኛ ውጤት የተገኘበት መሆኑን ያነሱት ኃላፊው የሰብል ልማትም ተጠናክሮ መቀጠሉን አንስተዋል። ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ ለምርቱ ከ384 የሸማች ማበራት ጋር የገበያ ትስስር መፈጠሩን ገልጸዋል። የመስኖ ልማቱ የአርሶ አደሩን ኑሮ ከማሻሻሉ በላይ ገበያን በማረጋጋት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን አክለዋል።
በዞኑ በመጪው ክረምት በ884 ሔክታር መሬት ላይ የሻይ ቅጠል ችግኝ ይተከላል 
Apr 30, 2026 115
መቱ፤ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በኢሉአባቦር ዞን በመጪው ክረምት በ884 ሔክታር መሬት ላይ 13 ነጥብ 8 ሚሊዮን የሻይ ቅጠል ችግኝ ለመትከል እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ አዳሙ ታከለ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ህብረተሰቡ ከሌሎች የግብርና ስራዎች ጎን ለጎን በሻይ ልማት ኢንሼቲቭ ተጠቃሚ እንዲሆን በትኩረት እየተሰራ ነው። በዚህም ዘንድሮ በ884 ሄክታር መሬት ላይ የሻይ ቅጠል ችግኞችን ለማልማት ታቅዶ የችግኝና የጉድጓድ ቁፋሮ ዝግጅት ስራ በሰፊው እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በተያዘው ዓመትም 18 ነጥብ 5 ሚሊዮን ችግኞችን ማዘጋጀት እንደተቻለ የተናገሩት ኃላፊው፣ ከዚህም ውስጥ 13 ነጥብ 5 ሚሊዮን የሻይ ቅጠል ችግኞች በመጪው ክረምት በ884 ሔክታር መሬት ላይ እንደሚተከሉ ገልፀዋል። የልማት ስራው በዞኑ ስድስት ወረዳዎች በሚገኙ 22 ቀበሌዎች እየተከናወነ ሲሆን፣ አርሶ አደሮችና የጥቃቅንና አነስተኛ ማህበራትን ጨምሮ ከ400 በላይ ዜጎች በልማቱ እየተሳተፉ መሆኑን ጠቁመዋል። በዞኑ በሻይ ልማት ግብርና ስራ ላይ የተሰማሩ አርሶአደሮችም የሻይ ልማት ስራ በሁሉም ደረጃ በአብዛኛው በሰው ኃይል የሚሰራ በመሆኑ ለበርካቶች የስራ ዕድልን እንደሚፈጥር አስረድተዋል። በሌላ በኩል ለምርት ደረጃ ሲደርስ በየሁለት ሳምንቱ እየተለቀመ ለፋብሪካ የሚቀርብ በመሆኑ ቋሚ የገቢ ምንጭ እንደሚሆንም ገልጸዋል። ለሌሎች የስራ እድሎችን እየፈጠሩ ለራሳቸውም ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ ጠንክረው እየሰሩ መሆናቸውንም ነው አርሶአደሮቹ የገለጹት።
በጋሞ ዞን በበጋ መስኖ ስንዴ ከለማ ማሳ ከ44 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ተሰበሰበ 
Apr 30, 2026 100
አርባ ምንጭ፤ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡-በጋሞ ዞን በበጋ መስኖ ስንዴ ከለማው 1ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ ከ44 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ሃላፊ አቶ ወርቅነህ ካልሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ በ13 የዞኑ ወረዳዎች 1ሺህ 380 ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ለምቷል። ከልማቱም ከ44 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱንና የምርታማነት መጠንም በሄክታር በአማካይ 32 ኩንታል መድረሱን ተናግረዋል። የበጋ መስኖ ስንዴ ልማቱ ሙሉ የግብርና ፓኬጅ በመጠቀም መከናወኑን አስታውሰው፣ ለልማቱ በአጠቃላይ 2ሺህ 760 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያና ዩሪያ ጥቅም ላይ ውሏል ብለዋል። በምዕራብ አባያ ወረዳ የሳውዝ አግሪ ድርጅት ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ብሩክ ከበደ፣ ድርጅቱ በ20 ሄክታር መሬት ላይ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ማከናወኑን ገልጸው፣ ምርታማነትም በሄክታር 35 ኩንታል ደርሷል ብለዋል። በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት እየተገኘ ያለው ምርት የአካባቢው አርሶ አደሮችን በማነቃቃት በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ተናግረዋል። የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከዚህ ቀደም በአካባቢያቸው ባይለመድም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በልማቱ በመሳተፍ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን የገለጹት ደግሞ በቁጫ ወረዳ የፋንጎ ቀበሌ ሞዴል አርሶ አደር ሚሊዮን በየነ ናቸው። ዘንድሮ በበጋ ወቅት በሁለት ሄክታር መሬት ላይ በመስኖ ካለሙት ስንዴ 66 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። በልማቱ የሚያገኙት ምርት የቤት ውስጥ ፍጆታቸውን ከመሸፈን ባለፈ ገቢያቸውን ለማሳደግ እያገዛቸው መሆኑንም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም