ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የሀዋሳ ከተማ የተቸረችውን የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ አልምቶ ለመጠቀም በተከናወኑ ተግባራት ውጤት ተመዝግቧል
Sep 10, 2026 163
ሀዋሳ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የሀዋሳ ከተማ የተቸረችውን የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ አልምቶ ለመጠቀምና ለህዝብ ጥቅም ለማዋል በተከናወኑ ተግባራት ውጤት መመዝገቡን ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለጹ፡፡ የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ግንባታ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የምስጋናና የዕውቅና መርሀ ግብር እየተካሔደ ነው። ''ሀዋሳ ታመሰግናችኋለች'' በሚል መሪ ቃል የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞና ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ሀላፊዎች በተገኙበት ነው መርሃ ግብሩ እየተካሔደ የሚገኘው። የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ እንደገለጹት በ2018 በጀት ዓመት የታቀዱ ተግባራት በቅንጅት ተከናውነው ውጤት ያስገኙበት ነው። ከተማዋ የተቸረችውን የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ አልምቶ ለመጠቀምና ለህዝብ ጥቅም ለማዋል የተደረገው ጥረት ተስፋ ሰጪ ውጤት ማስመዝገቡን አንስተዋል። ከእነዚህም አንዱ የሐይቅ ዳር ልማት ፕሮጀክት መሆኑን አንስተው በመንግስትና በአጋር አካላት ተሳትፎ ግንባታው እየተፋጠነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ የከተማዋን ገጽታና ውበት እንዲሁም ተወዳዳሪነትና ተመራጭነትን በማሳደግ ረገድ ትርጉም ያለው ውጤት እንደሚኖረው ተናግረዋል። በዚህ የልማት ሥራ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ የሚገኙ አካላትን ያመሰገኑት ከንቲባው የዛሬው የምስጋናና ዕውቅና መርሀ ግብር የተዘጋጀው ተሳትፎውን የበለጠ ለማጠናከር መሆኑን አስረድተዋል። በመርሀ ግብሩ ላይ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ ካቢኔ አባላት፣ባለሀብቶች፣የሀገር ሽማግሌዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
በግንባታ ላይ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ለነገዋ ኢትዮጵያ ጠንካራ መሰረት የሚያኖሩ ናቸው- ወጣቶች
Sep 10, 2026 112
ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ በግንባታ ላይ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ለነገዋ ኢትዮጵያ ጠንካራ መሰረት የሚያኖሩ መሆኑን በሀዋሳ ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው ወጣቶች ገለጹ። ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቁን ተከትሎ ሌሎች የሀገርን እድገትና ብልጽግና ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች በመከናወን ላይ ይገኛሉ። በግንባታ ላይ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያን በላቀ መልኩ ወደ ፊት የሚያራምዱ እና ለቀጣዩ ትውልድ ብሩህ ተስፋ የሰነቁ መሆናቸው ይታመናል። የነገዋን ኢትዮጵያ የሚወስኑት እነዚህ የልማት ፕሮጀክቶች ከሀገራዊ ፋይዳም የተሻገረ ቀጣናዊና አህጉራዊ ጠቀሜታ የሚኖራቸው ናቸው። ከግዙፍ ፕሮጀክቶቹ መካከል የቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ፣ የኒውኩለር ማብላያ፣ የጋዝ ፋብሪካ፣ ማዳበሪያ ፋብሪካ፣ የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ይጠቀሳሉ። እነዚህ ግዙፍ ፕሮጀክቶችና ሌሎችም እየተከናወኑ ያሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች የነገዋ ኢትዮጵያ ፅኑ መሰረትና የትውልዱ ብሩህ ተስፋ የሚሆኑ ናቸው። በሌላ በኩል ወጣቱን ትውልድ በቴክኖሎጂ ተጠቃሚ በማድረግ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆን ለማስቻል እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች የነገዋን ኢትዮጵያ ለመገንባት መሰረት የሚጥሉ ናቸው። በፖለቲካና ዲፕሎማሲ መስኮች የሚከናወኑ ሀገራዊ ጉዳዮችም የነገዋን የበለጸገች ኢትዮጰያ ለመገንባት ተስፋ የተሰነቀባቸው መሆኑን መግለፅ ይቻላል። ከዚሁ ጋር በተገናኘ ኢዜአ ያነጋገራቸው የሀዋሳ ከተማ ወጣቶች በመደመር መንግስት እየተከናወኑ ያሉ ሀገራዊ ኢንሼቲቮችና ግዙፍ ፕሮጀክቶች የነገዋ ኢትዮጵያ ጠንካራ መሰረቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወጣት በቃሉ መሠረት፤ ታላቁ የህዳሴ ግድብ፣ የጉባ ብስራቶች፣ የገበታ ፕሮጀክቶች፣ የኮሪደር ልማት ሥራዎችና ሌሎች ሀገራዊ ፕሮጀክቶች ዛሬን ብቻ ሳይሆን ነገንም ጭምር ታሳቢ ያደረጉ መሆናቸውን አንስቷል። የኢትዮጵያ የወደፊት እጣ ፈንታ ላይ ለመወሰን በተለይም የወጣቶች ጠንካራ ተሳትፎ አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሶ በዲጂታል ዘርፍ ግንባር ቀደም ተሳታፊ የሚሆንበት መደላድል መፈጠሩ ጥሩ ጅምር መሆኑን ተናግሯል። ሌላኛው ወጣት ኃይለኢየሱስ ታምራት፤ በመደመር መንግስት እየተከናወኑ ካሉ ነገን ታሳቢ ያደረጉ ተግባራት መካከል የጠንካራ ተቋማት ግንባታ ሥራዎች ኢትዮጵያን ሊያሻግሩ የሚችሉ ናቸው ብሏል፡፡ ለአብነት በስኬት መከናወን የቻለው ሀገራዊ ምክክር በመነጋገር ላይ የተመሰረተ አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍን የከፈተ ፣ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በዕኩልነት ለነገይቱ ኢትዮጵያ ሀሳብ ያዋጣበት መሆኑን ገልጿል፡፡ ወጣት ትዕግስት ፍስሀ በበኩሏ የመደመር መንግስት የኢትዮጵያ የህልውናና የነገ እጣ ፈንታ የሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮችንም በመተግበር በኢኮኖሚ የተሻለ ተወዳዳሪ የሆነች ሀገር ለመገንባት እየሰራ መሆኑን ተናግራለች፡፡ የባህር በር ባለቤትነትን ለማረጋገጥ አሁን ላይ እየተከናወኑ ያሉ ዓለም ዓቀፍ መርህን መሰረት ያደረጉ እንቅስቃሴዎች ኢትዮጵያን ከፍ የሚያደርጉ ተግባራት መሆናቸውን ጠቅሳለች፡፡ የባህር በር ባለቤትነት ለነገይቱ ኢትዮጵያ ዘርፈ ብዙ አንድምታ ያለው መሆኑን የተናገረችው ወጣት ትዕግስት፣ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠርና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞች በማስገኘት ረገድ ትልቅ ተስፋ የሚጣልበት ተግባር መሆኑን አመላክታለች፡፡ መንግስት በሁሉም ዘርፎች እያከናወናቸው ያሉ ስኬታማ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የበኩላቸውን እንደሚወጡ ወጣቶቹ አረጋግጠዋል፡፡
በኢትዮጵያ እየተመዘገበ ያለው ፈጣን እድገት በትውልዱ ዘንድ ብሩህ ተስፋ እና የላቀ ተነሳሽነት ፈጥሯል
Sep 10, 2026 110
ጂንካ፤ ጷግሜን 5/2018 (ኢዜአ፡-በኢትዮጵያ በየዘርፉ እየተመዘገበ ያለው ፈጣን እድገትና ለውጥ በትውልዱ ዘንድ ብሩህ ተስፋ እና የላቀ ተነሳሽነትን መፍጠሩን የጂንካ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተገነቡና በግንባታ ላይ ያሉ ሜጋ ፕሮጀክቶቹ የአሁኑን ትውልድ ብቻ ሳይሆን የመጪውን ብሩህ ጊዜ ታሳቢ ያደረጉ ስለመሆናቸውም ነዋሪዎቹ ተናግረዋል። "የነገ ቀን" ጳጉሜን-5 በሀገሪቱ በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ይገኛል፡፡ ቀኑን አስመልክቶ ኢዜአ በጂንካ ከተማ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች እንዳሉት ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ውስጥ እያስመዘገበች ያለው ፈጣን እድገትና ለውጥ ትውልዱ በነገዋ ኢትዮጵያ ቀን ብሩህ ተስፋ እንዲሰንቅ የላቀ ተነሳሽነት ፈጥሯል፡፡ ከነዋሪዎቹ መካከል የጂንካ ሁለተኛና መሰናዶ ትምህርት ቤት መምህር ሀብታሙ አያሌው እንዳሉት ሀገራችን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በግብርናው፣ በኢንዱስትሪ፣ በቴክኖሎጂና በቱሪዝም ዘርፎች ተጨባጭ የሆነ ፈጣን እድገት አስመዝግባለች። በሀገሪቱ የተገነቡና እየተገነቡ ያሉ ሜጋ ፕሮጀክቶች ለነገዋ ኢትዮጵያና ለዜጎቿ ብሩህ ተስፋ መሆናቸውን ገልጸው፣ የሕዳሴው ግድብ፣ የቢሸፍቱ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት፣ የአረንጓዴ ልማት ሥራዎችና ሌሎች ግዙፍ ፕሮጀክቶች ሀገራዊ እድገትን በማፋጠን በየዘመኑ ትውልድን ተጠቃሚ ያደርጋሉ ብለዋል። በተለይ በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር፣ በቱሪዝም ዘርፍ፣ በዲጂታል ኢትዮጵያ እና በገበታ ለሀገርና ለትውልድ የተከናወኑ ስኬታማ የልማት ተግባራት ተጨባጭ ለውጥ ያመጡና በትውልዱ ዘንድ ተነሳሽነትን የፈጠሩ ናቸው ብለዋል። ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ታምራት ምናስ፣ በኢትዮጵያ በመከናወን ላይ ያሉ ሜጋ ፕሮጀክቶች እና ዲጂታል ቴክኖሎጂ ለዜጎች ብዙ ተስፋና ዕድሎች ይዘው መጥተዋል ብለዋል። በሴራ ያጣነውን የባህር በር ባለቤትነት የማስመለስ ጥረትን ጨምሮ ኢትዮጵያ ያላትን ሀብት በማልማት ከድህነት እንድትወጣ በተከናወኑ ሥራዎች እየተመዘገበ ያለው ውጤት በትውልዱ ዘንድ ተስፋን የሚያጭር ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በየዘርፉ እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶች መጪው ዘመን ለኢትዮጵያ ብሩህ እንደሆና ያሳያሉ ያሉት አቶ ታምራት፣ የኢትዮጵያን አድገት በላቀ ተነሳሽነት እና ትጋት ለማስቀጠል የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁነታቸውን አረጋግጠዋል። ወጣት በቃህኝ ጥላሁን በበኩሉ በኢትዮጵያ እየተከናወኑ ያሉ ትላልቅ ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች በወጣቱ ዘንድ ተስፋን ያጫሩ እና ለነገ ተነሳሽነቱን የያሳደጉ ናቸው ብሏል። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተከናወኑ ሥራዎችና በመከናወን ላይ ያሉ ተግባራት ከሀጋራዊ ፋይዳቸው ባለፈ በተለይ ወጣቱን ከቴክኖሎጂ ጋር በማስተዋወቅ ተጠቃሚ እያደረጉ መሆናቸውን ተናግሯል። ወጣቱ በዲጂታል ኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ አቅሙን ከማሳደግ ባለፈ ለሥራ ዕድል ፈጠራ በማዋል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን እያሳደገ ጭምር መምጣቱንም ገልጿል። ኢትዮጵያ የተሻለች፣ የበለጸገች እና በቴክኖሎጂ ራሷን የቻለች ሀገር ለማድረግ ዛሬ እየተሰሩ ያሉ ሥራዎች የሀገሪቱን የነገ ብሩህ ተስፋ እያለመለሙ በመሆኑ መጠናከር እንዳለባቸው ተናግሯል።
የሞጆ ሎጂስቲክስ ማዕከል የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ማብሰሪያ፣ የቀጣናው ማስተሳሰሪያ እና የመደመር እሳቤ ፍሬ ማሳያ ነው
Sep 10, 2026 158
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የሞጆ ሎጂስቲክስ ማዕከል የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ማብሰሪያ፣ የቀጣናው ማስተሳሰሪያ እና የመደመር እሳቤ ፍሬ ማሳያ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ መርቀው በይፋ ሥራ አስጀምረዋል። በመርሀ ግብሩ ላይ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ፣ የኢፌዴሪ ጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል የሀገራችን የደም ስር ነው። የትራንስፖርትና የሎጂስቲክስ አገልግሎት ችግሮችን መፍታት የሚያስችል የማዕዘን ድንጋይ መሆኑን ገልጸዋል። ማዕከሉ የሁለንተናዊ ልማትና ብልፅግና ማረጋገጫ የመደመር መንግሥት ስኬት አይነተኛ ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘርፉን ማነቆ በተመለከተ የሰጡት አቅጣጫ ፍሬ ማፍራቱ ማሳያ ነው ብለዋል። የሞጆ ሎጂስቲክስ ማዕከል የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ማብሰሪያ፣ የቀጣናው ማስተሳሰሪያ እና የመደመር እሳቤ ፍሬ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ የሎጂስቲክ ማዕከል እናደርጋታለን ያሉት ቃል በተግባር እውን እንዲሆን ያስችላል ያሉት ሚኒስትሩ፤ በማዕከሉ ሁለት የባቡር መስመሮች መዘርጋታቸውን ተናግረዋል። የወጭና ገቢ ንግድ ዕቃዎችን የሚያስተናግዱ መጋዘኖች የያዘና በአንድ ጊዜ በርካታ የጭነት አገልግሎት መስጠት ያስችላል ብለዋል። አርሶ አደሮች ምርታቸው ሳይበላሽ ለውጭ ገበያ ማቅረብ የሚችሉበትን ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል።
የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል በመደመር እይታ የሚመራው መንግሥት በሁሉም ዘርፎች ምርትና ምርታማነትን እያሳደገ ለመሆኑ ትልቅ ማሳያ ነው
Sep 10, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ ፕሮጀክት በመደመር እይታ የሚመራው መንግሥት በሁሉም ዘርፎች ምርትና ምርታማነትን እያሳደገ ለመሆኑ ትልቅ ማሳያ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ ፕሮጀክትን መርቀው በይፋ ሥራ አስጀምረዋል። በዚሁ የምርቃት መርሃ ግብር ላይ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ፣ የኢፌዴሪ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ እንግዶች ተገኝተዋል። የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የመደመር መንግሥት ባለፉት ዓመታት በሁሉም ዘርፎች ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ ጥራት ያለው ምርት ለማምረት እንዲሁም ምርቶችን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ በብቃት ለማቅረብ የመደመር እይታን መሠረት አድርጎ ሲሠራ ቆይቷል። በግብርናና በኢንዱስትሪ ዘርፎች የሚመረቱ ምርቶች የሚፈለገውን የጥራት ደረጃ ጠብቀው ለገበያ እንዲቀርቡ በቂ የሎጂስቲክስ አቅርቦት አለመኖሩን አስታውሰዋል፡፡ ይህንን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ባለፉት ዓመታት በርካታ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቁመው፤ በተለይም ዘመናዊና በቂ የማከማቻ መጋዘኖች እንዲገነቡ፣ የመንገድ መሠረተ ልማቶች እንዲዘረጉ እና ለሎጂስቲክስ ዘርፉ አስፈላጊ የሆኑ ተሽከርካሪዎች እንዲቀርቡ መደረጉን ገልጸዋል። ከዚህም በተጨማሪ እንደ አቮካዶና ሙዝ ያሉ በቀላሉ የሚበላሹ የግብርና ምርቶችን ጥራታቸውን ጠብቆ ወደ ውጭ ገበያ ለመላክ የሚያስችሉ የቀዝቃዛ ኮንቴይነሮችን ለማቅረብ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ዛሬ በሞጆ ተመርቆ ሥራ የጀመረው ፕሮጀክት በምርታማነት ዘርፍ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍትና የኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ከፍ የሚያደርግ ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የሀገርን ቀጣይ ተስፋ እና የትውልዱን እጣ ፋንታ የተሻለ ለማድረግ የዛሬው ብርታትና ትጋታችን ወሳኝ ነው- ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Sep 10, 2026 77
ባሕርዳር፤ ጳግሜ 5/ 2018 (ኢዜአ) ፡-የሀገርን ቀጣይ ተስፋ እና የትውልዱን እጣ ፋንታ የተሻለ ለማድረግ የዛሬው ብርታትና ትጋታችን ወሳኝ ነው ሲሉ የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። ጳጉሜን 5 የነገው ቀን በአማራ ክልል በተለያዩ መርሃ ግብሮች እየተከበረ ይገኛል። በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርእሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደ፤ የነገውን የሀገርን ተስፋ እና የትውልዱን እጣ ፋንታ የተሻለ ለማድረግ የዛሬው ብርታትና ትጋታችን ወሳኝ ነው ብለዋል። የዛሬው ትጋታችን ለነገ ከተስፋም ባለፈ ፍሬ የሚያፈራ በመሆኑ በሁሉም ረገድ የጀመርናቸው የልማት ስራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አፅኖት ሰጥተዋል። የክልሉ መንግሥት የነገውን ትውልድና የሀገር ተስፋ በማሰብ የአሻጋሪ ዕድገት እና የዘላቂ ልማት አቅዶችን ለማሳከት የተቀናጀ ጥረት እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የነገ ዋስትናችን ዛሬ በመሆኑ የቀጣዩን ትውልድ ተስፋ ለማሳመር በቴክኖሎጂና ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ላይ በማተኮር መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። ርእሰ መስተዳድሩ በማጠቃለያ መልእክታቸው አዲሱ ዓመት ለክልሉ ህዝብና ለመላው ኢትዮጵያዊያን የሰላም፣ የፍቅርና የስኬት እንዲሆን ተመኝተዋል።
በክልሉ የሚገኙ እምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት የዜጎችን ተጠቃሚነት እውን የማድረግ ጥረት ይቀጥላል
Sep 10, 2026 160
አሶሳ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሚገኙ እምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት ሁለንተናዊ እድገትና የዜጎችን ተጠቃሚነት እውን የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን በብልጽግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽህፈት ኃላፊ ኢሳቅ አብዱልቃድር ተናገሩ። የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ጳጉሜን 5 (የነገ ቀን) ምክንያት በማድረግ በአሶሳ ከተማ የግራናይት ፋብሪካ እና የቀርከሃ ፋብሪካዎች የስራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ላይ የተገኙት በብልጽግና ፓርቲ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኢሳቅ አብዱልቃድር፤ በክልሉ የተጀመሩ ሁለንተናዊ የልማት ስራዎች ትልቅ ተስፋ የተሰነቀባቸው መሆኑን ገልጸዋል። በጉብኝቱ ያረጋግጥነው ይህንኑ ነው ያሉት ሃላፊው በክልሉ የሚገኙ እምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት ሁለንተናዊ እድገትና የዜጎችን ተጠቃሚነት እውን የማድረግ ጥረት ይቀጥላል ብለዋል። በክልሉ በተለይም ወጣቶች የስራ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑና በዲጂታል ቴክኖሎጂ የዳበረ እውቀት እንዲኖራቸው ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። ባለፋት ዓመታት የተከናወኑ የልማት ስራዎች የነገዋን ኢትዮጵያ የብልጽግና ጉዞ የሚያረጋግጡ መሆናቸውን እና የዜጎችን ተጠቃሚነት በተግባር ያሳዩ መሆናቸውንም ገልጸዋል። በክልሉ የግብርናውን፣ ማዕድንና የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት እየተመዘገበ እንደሆነም ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ በክልሉ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ጉዞ እና የኢንቨስትመንት አማራጮችን ማልማት ላይ ያተኮረ የፓናል ውይይት ተካሂዷል።
ኢትዮጵያን የአፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራትን አጠናክረን እንቀጥላለን-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 10, 2026 111
ኢዲስ አበባ ፤ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያን የአፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራትን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያን ዕድገትና ልማት ሊያስቆሙ የሚሞክሩ ኃይሎችን ከማይችሉት ተራራ ጋር እየታገሉ መሆኑን በተግባር እናሳያቸዋልን ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያን መርቀው በይፋ ስራ አስጀምረዋል። በመርሀ ግብሩ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ፣ የኢፌዴሪ የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ባስተላለፉት መልዕክት ኢትዮጵያን የአፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራትን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። ባለፉት ጥቂት ወራት የተመዘገቡ በርካታ ስኬቶች ለነገዋ ኢትዮጵያ መሰረት የሚጥሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል። በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ከ50 ሚሊዮን የሚልቁ ዜጎች ድምፅ በመስጠት ለቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የሚመራቸውን መንግሥት የመረጡበት፣ ከኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች የተውጣጡ አራት ሺህ ዜጎች በጋራ መክረውና ዘክረው የኢትዮጵያን መፃኢ ጊዜ የወሰኑበት፣ ስምንት ነጥብ ሁለት ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል ጠቅላላ ድምሩን 56 ቢሊዮን ማድረስ የተቻለበት ዓመት መሆኑንም ተናግረዋል። እነዚህ የስምረት የድልና የመከናወን ስኬቶች ተሰናስለው ኢትዮጵያ ከ10 ነጥብ 2 በመቶ በላይ ዕድገት እንድታስመዘግብ አስችሏታል ብለዋል። እንደ ኢትዮጵያ ሰፊ ህዝብ ያለው ሀገር ለማደግ ሎጂስቲክስ ከፍተኛ ጉልበት እንዳለውም ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት። ሎጂስቲክስ ከትራንስፖርት፣ ወደብ፣ የባቡር መሰረተ ልማት ለአርሶ አደሩ እስከሚደርስ ያለውን ሰንሰለት የያዘ መሆኑን ገልጸው፤ ለኢትዮጵያ ዕድገት ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። የሎጂስቲክስ አገልግሎት ችግር የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ አንቆ የቆየ መሆኑን በማንሳት፣ የሞጆ ሎጂስቲክስ ማዕከል እነዚህን ችግሮች እንደሚፈታ ገልጸዋል። የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል የኮንቴነር የመያዝ አቅም ከ500 ሺህ ወደ አንድ ሚሊዮን ያሳድጋል ብለዋል። የኢትዮጵያ ዕድገት የተሟላ እንዲሆን ሁሉም ማዕዘናትን ከጫፍ ጫፍ ማገናኘት እንደሚገባ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያስገነዘቡት። በ2018 ዓ.ም የብዙ ድል፣ ስኬትና መከናወን ዘመን እንደነበር ገልጸው፤ በ2019 ዓ.ም የላቀ የምንፈፅምበት ዓመት እንደሚሆን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሰላም እንደሚሻሻል ጠቁመው፤ ከጀመርነው ዕድገትና ልማት ሊያስቆሙን የሚሞክሩ ኃይሎችን ከማይችሉት ተራራ ጋር እየታገሉ መሆኑን በተግባር እናሳያቸዋለን ሲሉም ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፤ኢትዮጵያን የአፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። ልጆቻችን የተሻለች ሀገር እንዲረከቡ ያለብንን አደራ በሙሉ ዕምነትና ብቃት እናከናውናለን ሲሉም ተናግረዋል።
አዲሱ ዓመት ሀገራዊ አንድነታችንን በማጠናከር በላቀ የስራ መንፈስ የተጀመሩ ሁሉን አቀፍ የልማት ስራዎች የሚጎለብቱበት ነው
Sep 10, 2026 70
ሐረር ፤ዻጉሜ 5/2018 (ኢዜአ) ፡-አዲሱ ዓመት ሀገራዊ አንድነታችንን በማጠናከር በላቀ የስራ መንፈስ የተጀመሩ ሁሉን አቀፍ የልማት ስራዎች የሚጎለብቱበት ነው ሲሉ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ተናገሩ፡፡ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በክልሉ “የነገ ቀን” በተከበረበት ዕለት አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ ባስተላለፉት መልዕክት የ2018 ልዩና ታሪካዊ ዓመት ነው ሲሉ ተናግረዋል። ለዚህም 7ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ፣ ዲሞክራሲያዊና ነፃ በሆነ መልኩ አካሂደን ህዝቡ የሥልጣን ባለቤትነቱን በድምፁ ያረጋገጠበት ታላቅ የዲሞክራሲ መድረክ ያካሄድንበት ነው ብለዋል። ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር በፍቅርና በጋራ የተሠራበት ማህበራዊ መሰረት በመጣሉ ሀገራዊ መግባባታችን መጎልበቱን ተናግረዋል፤ ለዘመናት የቆዩ መሠረታዊ ልዩነቶቻችንን በውይይትና በሰለጠነ መንገድ ለመፍታት፣ ብሔራዊ መግባባትን ለመገንባትና ለዘላቂ ሰላም መሠረት ለመጣል የተቻለበት ነው ብለዋል። ከፖለቲካና ዲሞክራሲያዊው ሂደት ጎን ለጎን፣ የዜጎቻችንን ህይወት የሚያሻሽሉ ታላላቅ የማህበራዊና የኢኮኖሚ ልማት ስራዎች በስፋት የተከናወኑበት ዓመትም ነው ሲሉ ገልጸዋል። ገፅታ የሚቀይሩ የኮሪደር ልማቶች፣ የቱሪዝም መስህቦችና ሰው-ተኮር ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁበት እንደነበረም አንስተዋል። የግብርናና የአካባቢ ልማት ስራ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ሀገራዊ የምግብ ዋስትናችንን እያረጋገጥን እንገኛለን ሲሉም ነው የተናገሩት። ዓመቱ ከፍተኛ መነሳሳትና ቁርጠኝነት የታየበት፣ የመላው ህዝባችን ንቁ ተሳትፎና ተጠቃሚነት የተረጋገጠበት መሆኑንም አንስተዋል። ቀጣዩ 2019 ዓ.ም ሀገራዊ አንድነታችንን የምናጠናክርበት፣ የሕግ የበላይነትን የምናረጋግጥበትና ጠንካራ የልማት መሠረት የምንጥልበት ዓመት ነው ብለዋል። የከተማና የገጠሩ ነዋሪ ህዝቦች ሁለንተናዊ እና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ልዩ ትኩረት ይሰጣቸዋል ሲሉ አስገንዝበዋል። በዚህም የከተማ እና የገጠር የኮሪደር እና የመሰረተ ልማት ስራዎች፣ የቅርስ እና የቱሪዝም መስህቦች ጥበቃ፣ የውበት እና ጽዳት ስራዎች፣ የመልሶ ማልማት፣ የግብርና ማዘመንና ምርታማነትን ማሳደግን ጨምሮ የቴክኖሎጂ ተጠቃሚነትን የማሳደግ ተግባራት ተጠናክረው የሚቀጥሉ ይሆናል ነው ያሉተ። የክልሉን ሰላምና የህግ የበላይነት ይበልጥ በማጠናከር የህዝቡን የመቻቻልና የአብሮነት እሴት የማጠናከር ስራም ትኩረት የሚሰጠው እንደሚሆን ነው ያብራሩት። በክልሉ ህዝቦች መካከል ለዘመናት ስር የሰደዱት የአብሮነት፣ የመከባበር፣ የወንድማማችነትና የእህትማማችነት አኩሪ እሴቶች በፀና አለት ላይ መትከልም የመደበኛ እቅዶች አካል እንደሚሆን ነው ያመለከቱት። የኑሮ ውድነት ጫናን የማቃለል፣ የስራ እድል ተጠቃሚነትን የማጎልበት፣ የግል ዘርፉ በኢንዱስትሪና አገልግሎትመስኮች ያለው ተሳትፎ እንዲጠናከር ይደረጋል ብለዋል። ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ከመሰረታቸው ለመንቀል ግልፅና ተጠያቂነት ያለው የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት መዘርጋትና የስራ ውጤታማነትን ማረጋገጥ ሌላው የአዲሱ ዓመት ቁልፍ ተግባራችን ነው ሲሉም ገልጸዋል። በመጨረሻም አዲሱ ዓመት የፍቅር፣ የመቀራረብ፣ የመተማመን፣ የአንድነት፣ የትጋት እና የብልፅግና ዓመት እንዲሆን ተመኝተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ60 ሄክታር መሬት ላይ የተገነባውን ዘመናዊ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ የመጀመሪያ ምዕራፍ መረቀው ከፈቱ
Sep 10, 2026 85
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ60 ሄክታር መሬት ላይ የተገነባውን ዘመናዊ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ የመጀመሪያ ምዕራፍ መረቀው ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ በሞጆ ተገኝተው በምረቃው ላይ ባስተላለፉት መልዕክት ግንባታውን ኢትዮጵያ የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ጉዞ፡ በተግባር የታነጸበት ስራ ሲሉ ገልጸውታል። ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት በዓመት እስከ 1 ሚሊዮን ባለ 20 ጫማ ኮንቴነሮችን የማስተናገድ አቅም ያላቸው ጣቢያዎችና ዘመናዊ መጋዘኖች ያሉት መሆኑንም ገልጸዋል። የደረቅ ብትን ጭነቶችን በሀገር ውስጥ እንድናሽግ ማስቻሉ፣ የውጭ ምንዛሬን ከመቆጠብ ባለፈ ለዜጎቻችን ሰፊ የሥራ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። የማዕከሉን የአሰራር ፍጥነት ለማሳደግ በሀገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ የተተከለው የባቡር ላይ ክሬን ከባቡር መስመር የሚደረገውን የኮንቴነር ዝውውር በከፍተኛ ፍጥነት ያከናውናል ሲሉም ገልጸዋል። ሙሉ አሰራሩ በዘመናዊ ዲጂታል መሰረተ ልማት የተሳሰረ በመሆኑ፣ ለተገልጋዮች ፈጣን እና አስተማማኝ አገልግሎትን ያሳልጣል። ይህ ማዕከል ከኢትዮ-ጅቡቲ መስመር ባሻገር ኢትዮጵያን፣ ደቡብ ሱዳንን እና ዩጋንዳን የሚያስተሳስረው የ‘ደሱ’ ኮሪደር አካል ሲሆን፤ ይህም ሀገራችን በዓለም አቀፍ የሎጂስቲክስ ደረጃ ላይ ያላትን ስፍራ የሚያሻሽልና የቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስራችንን ወደ አዲስ የዕድገት ምዕራፍ የሚያሸጋግር ትልቅ ድል ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር መመለስ ለዓለም አቀፍ የባሕር ላይ ንግድ መስመር ደህንነት አስፈላጊ ነው - በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሤ (ዶ/ር)
Sep 10, 2026 113
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር መመለስ ለዓለም አቀፍ የባሕር ላይ ንግድ መስመር ደህንነት እና ለቀጣናው ኢኮኖሚ ዕድገት አስፈላጊ መሆኑን በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሤ (ዶ/ር) ገለጹ። እስራኤል የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥያቄ የምትደግፈው መሆኑንም አስታውቀዋል። አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ እና እስራኤል ታሪካዊ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ወደ ላቀ አጋርነት እየተሸጋገረ ነው። በዚህም የመንግሥት ለመንግሥት፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እንዲሁም በንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ከፍተኛ ዕድገት እየተመዘገበ መሆኑንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በማደግ ላይ የምትገኝ ሀገር ናት ያሉት አምባሳደሩ፤ ለዚህም የኢትዮጵያን ወጪና ገቢ ንግድ የሚያሳልጥ የባሕር በር ከሌለ ዕድገትን ለማፋጠን አዳጋች ነው ብለዋል። ለዚህም ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነትን ለማረጋገጥ ላቀረበችው ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥረት እስራኤል በሙሉ ድጋፍ እንደምታደርግ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር መመለስ የባሕር ላይ ሽብርተኞችንና ወንበዴዎችን በመመከት ለዓለም ሰላም እና የኢኮኖሚ ዕድገት ጥሩ ውጤት የሚያመጣ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት የሁለቱን ሀገራት ጂኦ ስትራቴጂክ ተጠቃሚነትን በማጎልበት ቀጣናዊ የሽብር ስጋቶችን በአስተማማኝ ሁኔታ ለመቀልበስ ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረውም አምባሳደሩ አስረድተዋል። ሽብርተኞች በቀይ ባሕር ስትራቴጂክ የንግድ መስመር በመርከቦች ላይ በሚፈጽሙት ጥቃት ምክንያት በንግድ ስርዓቱ ላይ ሳንካ እየፈጠሩ መሆኑን ጠቁመዋል። የእነዚህ የሽብር ኃይሎች እንቅስቃሴ ከኢትዮጵያ እና እስራኤል ባሻገር ለአውሮፓ፣ አሜሪካ፣ እስያና ለሌሎች ሀገራትም ጭምር የደህንነት ስጋት መሆኑን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ መልስ ማግኘት መሰል የሽብር ኃይሎች እንቅስቃሴን በመግታት የኢኮኖሚና የደኅንነት ሉዓላዊነቷን ለማስጠበቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውም ነው አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ያመላከቱት። በመሆኑም የኢትዮጵያ አስተማማኝ ወደብ የማግኘት ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ተቀባይነት ያለውና እስራኤልም የምትደግፈው መሆኑን ጨምረው አረጋግጠዋል። በተጨማሪም የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነትና ወደ ቀይ ባህር የመመለስ ምክንያታዊ ጥያቄ የምስራቅ አፍሪካ ቀጣናን ሰላምና ደኅንነት ለማስጠበቅ ብሎም ቀጣናውን በመሰረተ ልማትና በኢኮኖሚ ለማስተሳሰር ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በየዓመቱ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቀነስ የሚያስችል አቅም እየፈጠረች እንደምትገኝም ገልጸዋል። እስራኤልም በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፎች ያላትን ልምድና ተሞክሮ በማጋራት ድጋፏን እንደምታጠናክር አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ብዝኅ የተፈጥሮ ሃብት፣ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና አምራች የሰው ሃይል ከእስራኤል ቴክኖሎጂና ፈጠራ ትብብር ጋር በማቆራኘት ፈጣን ዕድገት ማስመዝገብ እንደሚያስችላት አንስተዋል። ኢትዮጵያ በዓድዋ ድል ለአፍሪካውያን የነፃነት ምልክት እንደሆነችው ሁሉ፤ ድህነትንና ኋላ ቀርነትን በመግታት እንዲሁም በዲጂታል ሥርዓትና ብዝኅ ልማትም ፋና ወጊ መሆኗን ተናግረዋል።
የአዲስ አበባ ፈጣን የከተማ ለውጥ የሚያስደንቅ ነው - የጀርመኑ ዲፕሎማት
Sep 10, 2026 117
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ እየተከናወኑ ያሉ ሁሉን አቀፍ የከተማ ልማት ስራዎች መዲናዋን በከፍተኛ ፍጥነት እንድትለወጥ ማድረጋቸውን በኢትዮጵያ የጀርመን ተጠባባቂ አምባሳደር ፈርዲናንድ ቮን ዌይሄ ገለጹ። ዘመናዊ ኮሪደሮች፣ መልሰው ያገገሙ የወንዞች ዳርቻዎች፣ የህዝብ መዝናኛ ስፍራዎች እና እየሰፉ ያሉ አረንጓዴ ቦታዎች ለከተማዋ አዲስ መልክ መስጠታቸውን አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። ባለፉት ሶስት ዓመታት በአዲስ አበባ በቆዩባቸው ጊዜያት በከተማዋ የታዩ ለውጦች፣ በተለይም የኮሪደር ልማት ስራዎችንና ለህዝብ መዝናኛ ክፍት ቦታዎችን የማስፋት አጠቃላይ እንቅስቃሴን በቅርብ መከታተላቸውን ተናግረዋል። በቆይታቸው የታዩ ተጨባጭ ለውጦችን መመልከታቸውንም ገልጸዋል። የለውጡ ፍጥነት፣ የስራ ቁርጠኝነት እና ጥንካሬ የሚያስደንቅ መሆኑንም ነው የተናገሩት። በአዲስ አበባ የሚከናወኑ የተለያዩ የልማት ስራዎች እርስ በእርሳቸው የተሳሰሩ እና ሰፊ የከተማ ፕላን እቅድን መሰረት ያደረጉ መሆናቸውን ለመገንዘብ እንደሚቻልም አመልክተዋል። ሁሉም የኮሪደር ስራዎች እና የልማት እንቅስቃሴዎች አንዱ ከሌላው ጋር ተጣጥመውና ተቀናጅተው የሚከናወኑ መሆናቸውም የሚደነቅ ነው ብለዋል። በቀበና ወንዝ አካባቢ፣ ከጀርመን ኤምባሲ አቅራቢያ አንስቶ እስከ ፈረንሳይ ኤምባሲ ድረስ ያሉትን ቦታዎች በመጥቀስ፣ እነዚህ ስፍራዎች የከተማዋ ገጽታ መለወጥ መገለጫዎች መሆናቸውን ጠቁመዋል። ለውጦቹ በግንባታና በመሰረተ ልማት ላይ ብቻ የተወሰኑ እንዳልሆኑም ነው ያነሱት። አሁን ላይ በርካታ ነዋሪዎች ከሰዓት በኋላ ጊዜያቸውን ከቤት ውጭ በማሳለፍ፣ በወንዞች ዳርቻዎች የእግር ጉዞ በማድረግ እና ህጻናትም በአዲሶቹ የብስክሌት መንገዶች እየተጠቀሙ መሆኑ ትልቅ ለውጥ ነው ብለዋል። አምባሳደሩ የአዲስ አበባን የአረንጓዴ ልማት ስራዎች ከኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተሳሰሩ መሆናቸውን ነው ያነሱት። መርሃ ግብሩ የዛፍ ተከላ፣ የደን ልማት እና የአካባቢ ጥበቃን ከሀገሪቱ የልማት አጀንዳዎች ጋር የተቀናጀ መሆኑንም አድንቀዋል። በግላቸው በመቶዎች የሚቆጠሩ ዛፎችን መትከላቸውንም አስታውሰዋል። የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ስኬት የተመሠረተው ዛፍ በመትከል ሂደቱ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ ዛፉ እስኪጸድቅና ሙሉ ዕድገት እስኪያሳይ ድረስ በሚደረግ ቀጣይነት ያለው እንክብካቤ ላይ መሆኑን ከራሳቸው ተግባራዊ ልምድ መረዳታቸውን ገልጸዋል። ዛፍ መትከል ብቻ ሳይሆን ዛፉ እያደገ ሲሄድ አብሮ መንከባከብና መከታተልን ይጠይቃል ብለዋል።
በበዓል ገበያ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶች በቂ አቅርቦት በመኖሩ የተረጋጋ ግብይት እያካሄድን ነው -ሸማቾች
Sep 10, 2026 104
ሀዋሳ፣ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ):- በሀዋሳ ከተማ ለዘመን መለወጫ የበዓል ገበያ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶች በቂ አቅርቦት በመኖሩ የተረጋጋ ግብይት እያካሄዱ መሆናቸውንሸማቾች ገለጹ ። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር በበኩሉ የአዲስ አመት ዘመን መለወጫ በዓልን ታሳቢ ያደረገ አማራጭ የግብይት ማዕከላትን በማመቻቸት በቂ የምርት አቅርቦት እንዲኖር ማድረጉን አመልክቷል፡፡ ኢዜአ በከተማዋ በተለያዩ አከባቢዎች ተዘዋውሮ እንተደመለከተው የግብርናም ሆነ የኢንዱስትሪ ምርቶች በስፋት የቀረቡ ሲሆን በተመቻቹ አማራጭ የገበያ ማዕከላት ነዋሪዎች የበዓል ግብይታቸውን እያካሄዱ ናቸው። አስተያየታቸውን ከሰጡት ሸማቾች መካከል ወይዘሮ መቅደስ ካሳሁን አስተዳደሩ ባመቻቸው የአማራጭ ግብይት ማዕከላት በቂ የሆነ የፋብሪካና የኢንደስትሪ ምርት አቅርቦት መኖሩን ጠቅሰዋል። በገበያው ከመደበኛው የበዓል ቅናሽ ዋጋ በመኖሩ ሸቀጦችን በተረጋጋ ሁኔታ እየተገበያዩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በከተማዋ የግብርናም ሆነ የኢንዱስትሪ ምርቶች በጥሩ ሁኔታ በመቅረባቸው የዋጋ ሁኔታም የተረጋጋ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ሌላው ሸማች አቶ ኢሳያስ ከበደ የተባሉ ናቸው ። በመደበኛው ገበያና በአማራጭ የግብይት ማዕከላት በማህበራት በኩል ምርቶቻቸውን ማቅረባቸው ሁሉም እንደአቅሙ መሸመት የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። አስተዳደሩ ባመቻቸው የመሸጫ ቦታ ከመደበኛው ገበያ በቅናሽ ለሸማቹ እየሸጡ መሆኑን የተናገረችው ደግሞ ወይዘሪት ብሩክ ቃሬሶ ነች። የአዲስ ዘመን የበዓል ገበያ የተረጋጋ መሆኑን የተናገሩት የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ አጋና ነቶ ለዚህም የተደረጉ ቅድመ ዝግጅቶች የላቀ ሚና መጫወታቸውን ተናግረዋል። የበዓል ገበያውን የተረጋጋ ለማድረግ በምርት አቅርቦትና የዋጋ ቁጥጥርና ክትትል የሚያደርግ ከሰባት ተቋማትና የተለያዩ አካላት ያሉበት ግብረ ሀይል ተቋቁሞ ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል። በተለይም የምርት እጥረት እንዳይከሰት ከመደበኛ ገበያዎች በተጨማሪ አማራጭ የግብይት ማዕከላትን በማደራጀት አምራቹና ሸማቹ በቀጥታ የሚገናኙበት ሁኔታ በማመቻቸት ማህበረሰቡ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ መደረጉን ተናግዋል። የክትትልና ቁጥጥር ስርዓቱም በቅንጅት እየተሰራ እና በአጠቃላይ የበዓል ገበያ የተረጋጋ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ኢትዮጵያ ነገዋን ዛሬ እየሠራች ነው-የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
Sep 10, 2026 134
ነገ የሚወሰነው ዛሬ በምንሠራው ሥራ ነው! የነገ ስኬታችን የሚቀረጸው በዛሬው ጥረታችን ነው። ከትናንት መልካም ልምዶችን በመቅሰም፣ ዛሬን በትክክል አጢኖ የነገን ራዕይ ዛሬ ላይ ሆኖ መገንባት የመንግሥታችን ጽኑ እምነትና መለያ ባህሪ ነው። ሀገር በቀል ዕውቀትን ከዘመኑ ቴክኖሎጂ ጋር አስተሳስሮ ነገን ለመዋጀት መዘጋጀት ከዚህ ትውልድ የሚጠበቅ ትልቅ ኃላፊነት እንደኾነ መንግሥት በፅኑ ያምናል፡፡ ለዚህም ነው ዲጂታላይዜሽንን እንደ አስቻይም እንደ ኢኮኖሚ ዘርፍም በመውሰድ ትልቅ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ያለው፡፡ ኢትዮጵያ ለቀጣዩ ትውልድ ምንዳን እንጅ ዕዳን አታወርስም፡፡ ጊዜ በየአንጓዉ ለሚጠይቀዉ ጉዳይ ምላሽ መስጠት አለመቻል የትውልድ ዕዳ ነው፡፡ ለዚህም ነው ሀገራችን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ታዳጊዎችን በትምህርት ቤት እየመገበች የምታስተምረው፤ ለዚህም ነው በሚሊዮን የሚቆጠሩ ወጣቶችን በነፃ የኮደርስ ሥልጠና እያበቃች ያለችው፤ ለዚህም ነው የመጀመሪያውን የሰው ሠራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ እያቋቋመች ያለችው ፡፡ ነገ ያለቴክኖሎጂ ዕውቀት፣ ነገ ያለሳይበር ደኅንነት፣ ነገ ያለመረጃ ሉዓላዊነት የሕልውና አደጋ አንደኾነ መንግሥታችን ይገነዘባል፤ ትውልዱን ለዚያ ያዘጋጃል፡፡ ለዘመናት ኋላቀር ሲባል የነበረዉ የኢኮኖሚ ዘርፍ ግብርና ነገ ያለቴክኖሎጂ ሕልውናዉ አደጋ ላይ ነው፡፡ ለተፈጥሯዊ እና ሰው ሠራሽ አደጋዎች ቅድመ ጥንቃቄ እና ምላሽ አሰጣጥ ዲጂታላይዜሽን ወሳኝ ነው፡፡ የመንግሥት አገልግሎቶችን በጥራት እና በፍጥነት ለዜጎች ተደራሽ ለማድረግ ያለፉት ዘመናት አሠራሮች አይደለም ነገ ዛሬም አዋጭ አይደሉም፡፡ በዓለማቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እና ሥራ ፈጣሪ ወጣቶችን ለማፍራት ዲጂታል ክሕሎት በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ለእነዚህ ኹሉ ጉዳዮች ትኩረት ሰጥታ እየሠራች ስለምትገኝ ነው “ኢትዮጵያ ነገዋን ዛሬ እየሠራች ነው” የምንለው፡፡ የጳጒሜን አምስተኛ ቀን የነገ ቀን ብለን ማክበራችንም መጪዉ ዘመን የቴክኖሎጂ ተወዳዳሪነትን የሚጠይቅ፣ መረጃ ትንተና ላይ የተመሠረተ ውሳኔ የሚሰጥበት፣ ከግብርና እስከ ሕዋ ሳይንስ ምርምሮች በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዙ የሚኾኑበት ዘመን ዋዜማ ላይ ስለምንገኝ ለዚያ የሚመጥን ትውልድ ለማፍራት እንደምንሠራ ለማስገንዘብ ነው፡፡ ጳጉምን 5 የነገ ቀን በሚል ስያሜ መከበሩ ዲጂታላይዜሽን ለነገዋ ኢትዮጵያ ግንባታ እና ሉዓላዊነት መከበር ሀገራችን ወደ ዲጂታላይዜሽን ሽግግር ምዕራፍ ላይ እንደምትገኝ ለማብሰር ነው፡፡
ሜጋ ፕሮጀክቶች የነገዋን ኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ አቅም የሚገነቡ የልማት ማዕዘናት ናቸው
Sep 10, 2026 158
ጅማ ፤ጳጉሜ 5/2018 (ኢዜአ)፡-ሜጋ ፕሮጀክቶችና የመሠረተ ልማት ግንባታዎች የነገዋን ኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ አቅም በጠንካራ መሠረት ላይ ለመገንባት ከፍተኛ ፋይዳ እንዳላቸው ምሁራን ገለጹ። ኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የሀገሪቱን የልማት ምህዳር እና የከተሞች ገጽታ የሚቀይሩ በርካታ ግዙፍ የልማትና የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶችን በስፋት ስትተገብር ቆይታለች። ከእነዚህም መካከል ሀገሪቱን የንጹህ ኤሌክትሪክ ኃይል ማዕከል የሚያደርጋት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ የከተሞችን ጽዳት፣ ጤናማነትና የመሳብ አቅም ያሳደገው የኮሪደር ልማት፣ የወደፊት ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስን የሚያዘምኑ የኤርፖርትና የባቡር መስመር ማስፋፊያዎች፣ እንዲሁም በገበታ ለሀገርና ገበታ ለትውልድ ስር የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎች ይጠቀሳሉ። እነዚህ ፕሮጀክቶች ቀደም ሲል ይስተዋል የነበረውን የመሠረተ ልማት እጥረት በመቅረፍ፣ ለሚሊዮኖች የሥራ ዕድል በመፍጠርና የኢንዱስትሪ ሽግግርን በማፋጠን ረገድ የጎላ ሚና እያበረከቱ ይገኛሉ። በዚሁ ጉዳይ ላይ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የጅማ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን እንዳሉት፤ ሜጋ ፕሮጀክቶቹ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ከማሻሻል ባሻገር የክልላዊና ዓለም አቀፋዊ ተወዳዳሪነትን የሚያሳድጉ፣ ለስራ እድል ፈጠራና ለኢንዱስትሪ እድገት መንገድ የሚከፍቱ ስልታዊ የልማት እርምጃዎች ናቸው። በዩኒቨርሲቲው የሕግ እና አስተዳደር መምህር ደሊል አህመድ እንደገለጹት፤ በሀገሪቱ በተለያዩ ዘርፎች እየተከናወኑ ያሉ ግዙፍ የልማት ሥራዎች የኢትዮጵያን የወደፊት ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ አቅም ለመገንባት ጠንካራ መሠረት እየጣሉ ይገኛሉ። በተለይም የታላቁ ህዳሴ ግድብ ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳው ባሻገር የኢትዮጵያውያን አንድነትና ብሔራዊ ኩራትን የሚያሳይ ምልክት መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም በከተሞች እየተካሄዱ የሚገኙት የኮሪደርና የመዝናኛ ስፍራዎች ልማት የቱሪዝም ዘርፉን ለማስፋፋት፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠርና የከተሞችን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለማነቃቃት የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆናቸውን መምህር ደሊል አስረድተዋል። መምህር ደሊል እንደገለጹት፣ የተጀመረው የልማት ጉዞ ዘላቂነት እንዲኖረው ሰላምን ማስከበርና የልማት እንቅስቃሴዎችን ማገዝ ያስፈልጋል። በሌላ በኩል በዩኒቨርሲቲው የሚዲያና ኮሙኒኬሽን መምህር ጌታቸው ጥላሁን (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የኃይል ማመንጫ፣ የመንገድና የአየር ማረፊያ ግንባታዎችን ጨምሮ ትልልቅ የልማት ፕሮጀክቶች ከተማን ከገጠር በማስተሳሰር የሕዝብን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን ለማፋጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ አላቸው። ጌታቸው(ዶ/ር) አክለውም፣ አሁን በተጣለው ጠንካራ መሠረት ላይ በመነሳት የነገዋን ኢትዮጵያ የመገንባቱ ሂደት በተማረና በብቁ የሰው ኃይል ላይ የሚመሠረት እንደሚሆን ገልጸዋል። ከታችኛው የትምህርት ደረጃ ጀምሮ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ድረስ ያሉትን ማዕከላት ማጠናከር፣ ወጣቶችን በዕውቀት፣ በሙያ ብቃትና በሥነ-ምግባር ለማነጽ የሚደረገውን ጥረት የሚያፋጥንና ለሀገሪቱ የወደፊት ዕድገት ወሳኝ መሆኑንም ጠቁመዋል። በተጨማሪም ጠንካራና ተጠያቂነት ያላቸው ተቋማት መኖር የነገዋን ኢትዮጵያ ከመገንባት አኳያ ወሳኝ መሆኑን ጌታቸው (ዶ/ር) ገልጸዋል። በተለይም የዴሞክራሲ፣ የሕግና የሚዲያ ተቋማት ነፃና ጠንካራ ሆነው ተጠያቂነትን እንዲያረጋግጡ ማድረግ፣ የሕግ የበላይነትን ማስከበርና ሙስናን መዋጋት ለሀገሪቱ መረጋጋትና ለኢኮኖሚ ዕድገት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወቱ አስረድተዋል። ምሁራኑ አክለው እንዳመለከቱት፤ ኢትዮጵያ በልማት ሥራዎች፣ በሰው ኃይል ግንባታና ተቋማትን በማጠናከር ረገድ የምታደርገው ጉዞ የተሻለ ነገን ለመገንባት ተስፋ ሰጪ ናቸው። ይህ ጉዞ ዘላቂ ውጤት እንዲያመጣ ግን ሰላምን፣ ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን፣ የሰው ኃይል ልማትንና ጠንካራ ተቋማትን በተጓዳኝ ማጠናከር እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የግብርናና የምግብ ሥርዓትን ማጠናከር ለአፍሪካ ዘላቂ ልማት ወሳኝ ነው
Sep 9, 2026 178
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ)፦የግብርናና የምግብ ሥርዓትን ማጠናከር አፍሪካ የአየር ንብረት ጫናን በመቋቋም ዘላቂ ልማቷን እንድታሳድግ ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ። በአዲስ አበባ ከተማ ከጳጉሜን 2 እስከ 4 ቀን ሲካሄድ የቆየው አህጉራዊ ጉባኤ ፍጻሜውን አግኝቷል። በጉባኤው ወቅት በአፍሪካ የግብርናና የምግብ ሥርዓትን ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር በማጣጣም የሕዝቦችን የምግብ ዋስትና እና የኑሮ ጽናት ለማሻሻል የሚያስችሉ ዋና ዋና አቅጣጫዎች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል። በዚሁ መድረክ ከ30 በላይ የአፍሪካ ሀገራት የተወጣጡ ተሳታፊዎች የተገኙ ሲሆን የአህጉሪቱን የግብርናና የምግብ አጀንዳ በዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ውይይቶች የበለጠ ማስገንዘብና ውሳኔዎችንም ወደ ተግባር ማሸጋገር በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ መክረዋል። የአፍሪካ የምግብ ሉዓላዊነት ህብረት (Alliance for Food Sovereignty in Africa - AFSA) አስተባባሪ ዶክተር ሚሊዮን በላይ እንደገለጹት፤ አፍሪካ በግብርናና በምግብ ሥርዓት ያላትን የራሷን ልምድና መፍትሔ በማጠናከር በአህጉርና በዓለም አቀፍ መድረኮች የራሷን አጀንዳ በተግባር ማስፈጸም ይገባታል። አህጉሪቱ በዘርፉ ያላትን መልካም ተሞክሮ የበለጠ ማጉላት እንዳለባት ጠቁመው ለተቋቋሚ የምግብ ሥርዓት ግንባታ አግሮ-ኢኮሎጂን ማስፋፋት፣ የገበሬዎችን የዘር ሀብት መጠበቅና የገበሬዎችን ተሞክሮ ከሳይንስ ጋር በማጣመር የተሻለ የግብርና ልማት ማምጣት እንደሚገባ አስረድተዋል። በተጨማሪም የአፈርና የውሃ ሀብትን በአግባቡ መጠቀም፣ የአካባቢ የምግብ ገበያዎችን ማጠናከርና አፍሪካ የምግብ ፍላጎቷን በተቻለ መጠን በራሷ ምርትና ሀብት በመሸፈን የምግብ ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ እንደሚገባት ገልጸዋል። የምግብ ሥርዓቱ ቀጥተኛ ተዋናዮች ሀሳባቸው በውሳኔዎች ውስጥ እንዲንጸባረቅ የሚያስችል ተጨባጭ ተሳትፎ ሊኖራቸው እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ በዘር ሀብት ጥበቃ፣ በአግሮ-ኢኮሎጂና በምግብ ሉዓላዊነት ያላትን ልምድ በማጠናከር ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ ማካፈል እንደምትችል ጠቁመዋል፡፡ የአርሶ አደሮችን የዘር ሀብት መጠበቅና አሀጉራዊ ተሞክሮዎችን ከሳይንሳዊ እውቀት ጋር በማጣመር የተሻለ የግብርና ልማት ለማስመዝገብ መስራት እንደሚገባ አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከዕዳ ተላቆ ወደ ውጤታማ የትርፋማነት ምዕራፍ ተሸጋግሯል - ኢንጂነር አሸብር ባልቻ
Sep 9, 2026 133
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከነበረበት ዕዳ ተላቆ ወደ የትርፋማነት ምዕራፍ መሸጋገሩን የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ አስታወቁ። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አመራርና ሠራተኞቹ በተገኙበት የዘንድሮውን የ2018 በጀት ዓመት "ንጹህ ኢነርጂ ለተሻለ ሕይወት" በሚል መሪ ሐሳብ የተቋም ቀኑን አክብሯል። ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ በዚህ ወቅት፤ ኤሌክትሪክ ኃይል ኢትዮጵያን የአፍሪካ የታዳሽ ኃይል ማዕከል የማድረግ ራዕይ የሚያሳካ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በ2018 በጀት ዓመት በርካታ የኃይል መሠረተ ልማት ፕሮጀክቶችን፣ የኦፕሬሽንና የጥገና ሥራዎችን በመሥራት ተቋማዊ የመፈጸም አቅምን ማላቅ መቻሉን አስታውቀዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ የአሰላና የአይሻ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች መጠናቀቅ ኃይል የማመንጨት አቅምን ወደ 9 ሺህ 730 ሜጋ ዋት በማሳደግ የ23 በመቶ ዕድገት እንዲመዘገብ ማስቻሉን ተናግረዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም ጠቅላላ የኃይል ምርት አቅም 35 ሺህ 671 ጊጋ ዋት በሰዓት በማድረስ የ124 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘት እንደተቻለ አስረድተዋል። ከኃይል ሽያጭና ዳታ ማይኒንግ 475 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ መገኘቱም የተቋሙን የገቢ አቅም ከባለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ64 በመቶ ዕድገት እንዲመዘገብ አስችሏል ብለዋል። በአጠቃላይ በበጀት ዓመቱ 39 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ በማስመዝገብ ተቋሙ ለመጀመሪያ ጊዜ ከዕዳ ወደ ትርፋማነት የተሸጋገረበትን ስኬታማ ዘመን እንዳሳለፈ ጠቅሰዋል። በዚህም የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከነበረበት ዕዳ ተላቆ ወደ ውጤታማ የትርፋማነት ምዕራፍ መሸጋገሩን አብስረዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ላስመዘገበው ስኬትም የተቋሙ አመራር፣ ሠራተኞችና ባለድርሻ አካላት ሚና የላቀ መሆኑን በማንሣት ለዚህ ሁሉንም አመስግነዋል። ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም የሁሉም ዜጎች ኩራትና አሻራ ያረፈበት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ተጠናቆ በይፋ የተመረቀበት ታሪካዊ ዕለት መሆኑንም አስታውሰዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የተቋም ቀንም የሕዳሴን ታሪካዊ ፍጻሜ በመዘከር የላቀ አፈጻጸም ለነበራቸው አመራርና ሠራተኞች ዕውቅና ለመስጠት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም በየዓመቱ ጳጉሜን 4 የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የተቋም ቀን ሆኖ እንደሚከበር አስታውቀዋል።
የእስያ መሰረተ ልማት ኢንቨስትመንት ባንክ የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት ስራዎች ለመደገፍ ያለውን ቁርጠኝነት አረጋገጠ
Sep 9, 2026 97
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ):- የእስያ መሰረተ ልማት ኢንቨስትመንት ባንክ የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት አጀንዳዎች እንደሚደግፍ አስታወቀ። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ አዲሷን የእስያ መሠረተ ልማት ኢንቨስትመንት ባንክ (AIIB) ፕሬዝዳንት ዙ ጂያዪን ዛሬ በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል። በውይይቱ ላይ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው ተሳትፈዋል። የሁለቱ ወገኖች ውይይት ባንኩ በቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ላይ ሊኖረው የሚችለውን ተሳትፎ ጨምሮ በአበይት የኢትዮጵያ የልማት ትኩረቶች ላይ ያተኮረ ነው። ከዚህም ባሻገር በኢነርጂ ዘርፍ እና የአየር ንብረት ለውጥን በሚከላከሉ ፕሮጀክቶች ዙሪያ ያላቸውን አጋርነት ማሳደግ፣ በዝቅተኛ ወለድ የሚሰጡ የብድር አቅርቦቶችን ማመቻቸት እንዲሁም ከሌሎች ባለብዙ ወገን የልማት ባንኮች ጋር በቅንጅት መሥራት በሚቻልበት ሁኔታ ላይም መክረዋል። በውይይቱ ወቅት የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ለፕሬዝዳንት ዙ ጂያዪ የኢትዮጵያ ሪፎርም አጀንዳ አፈጻጸም እና እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ያሉ ግዙፍ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ረገድ የተመዘገቡ ስኬቶችን አስመልክቶ ገለጻ አድርገዋል። ሚኒስትሩ አክለውም ባንኩ ኢትዮጵያ ቅድሚያ የምትሰጣቸውን የልማት ትኩረቶች መደገፍ የሚችልባቸውን የፋይናንስ አማራጮች አቅርበዋል። ፕሬዝዳንት ዙ ጂያዪ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በቀጣናው የኃይል ትስስርን በማስፋት ረገድ እየተወጣች ያለውን ግንባር ቀደም ሚና አድንቀዋል። ባንኩ የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት አጀንዳ ለመደገፍ ያለውን ቁርጠኝነትም አረጋግጠዋል። ሁለቱ ወገኖች አጋርነታቸውን በማጎልበት፤ ዘላቂና አሳታፊ የመሰረተ ልማት ዕድገትን በጋራ እውን ለማድረግ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል። የእስያ መሠረተ ልማት ኢንቨስትመንት ባንክ (AIIB) ፕሬዝዳንት ዙ ጂያዪ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋዊ የስራ ጉብኝት እያደረጉ እንደሚገኝ የገንዘብ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እና ሀገራዊ ምክክር ጉባዔ የመቻልና የአንድነት ሕብራዊነት መገለጫዎች ናቸው
Sep 9, 2026 131
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ) ፦ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እና ሀገራዊ ምክክር ጉባዔ ኢትዮጵያውያን በትብብር ያሳኳቸው የመቻልና የአንድነት ሕብራዊነት መገለጫዎች መሆናቸውን የሰላም ሚኒስቴር ገለጸ። የሰላም ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ሃላፊ መብራቱ ካሳ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በአንድነት ማሰሪያ የተጋመዱ ናቸው። ኢትዮጵያውያን የተጋመድን ነን ሲባል ከቃል ባለፈ በዓድዋ ጦርነትና በሌሎች ሀገራዊ ሉዓላዊነትን ለመዳፈር በተቃጡ ጥቃቶች ላይ በመተባበር በተግባር አሳይተናል ብለዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የጋራ የላብ፣ የደምና የውሃ ጠብታ ውጤት መሆኑን በመግለጽ፤ የኢትዮጵያውያን በጋራ መቻልን ያሳያል ብለዋል። ኢትዮጵያውያን ከማንኛውም አካል ተፅዕኖ ነጻ በመሆን ራሳቸውን በራሳቸው መለወጥ ማሳደግና ማበልጸግ እንደሚችሉ ያሳዩበት የሕብራዊነት መገለጫ ነው ሲሉም ተናግረዋል። በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ጉባዔ በህዝቦች መካከል የዘመናት ቁርሾ ሆነው የቆዩ ልዩነቶችን በምክክር መፍታት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያን የጋራ ችግራቸውን በራሳቸው አቅም በምክክር ለመፍታት ያሳዩት ቁርጠኝነት ለጠንካራ ሀገረ መንግሥት ግንባታ ያላቸውን ቀናኢነት ያሳያል ብለዋል። ሀገራዊ ምክክር ጉባዔው ኢትዮጵያ የራሷን ችግር በራሷ እየፈታች ያለች ሀገር መሆኗን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በተግባር ያረጋገጠ መሆኑንም ገልጸዋል።
በአማራ ክልል ለዘመን መለወጫ በዓል በቂ የእርድ እንስሳትና ሌሎች ምርቶች ቀርበዋል
Sep 9, 2026 111
ባህር ዳር ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ) ፦ በአማራ ክልል ለዘመን መለወጫ በዓል የእርድ እንስሳትና ሌሎች ምርቶችን በበቂ መጠን ለተጠቃሚው ማቅረብ መቻሉን የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ አትክልት አሳቤ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለዘመን መለወጫ በዓል በበቂ መጠን የእርድ እንስሳት፣ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች መቅረባቸውን ገልጸዋል። ምርቶቹን ከኢንዱስትሪዎች፣ ከግብርና አምራቾች፣ ከኢንተርፕራይዞች፣ ከህብረት ሥራ ማህበራት እንዲሁም ከእንስሳትና አሳ ሀብት ተቋማት ጋር በመቀናጀት በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል። በተለይም በትላልቅ ከተሞች በተገነቡ 2ኛ ደረጃ የገበያ ማዕከላት፣ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን ለሸማቹ በቀጥታ እንዲቀርብ መደረጉንም አስረድተዋል። በበዓሉ ወቅት የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይኖር ቀደም ብሎ በቂ ዝግጅት በመደረጉ፣ ህብረተሰቡ በአቅራቢያው እንዲገበያይ መደረጉንም ነው ያብራሩት። እስካሁን ባለውም ከ700 ሺህ በላይ የደለቡ ዳልጋ ከብቶች፣ በጎችና ፍየሎች እንዲሁም ከሁለት ሚሊዮን በላይ የስጋ ዶሮዎች ለበዓል ገበያ እንዲቀርቡ ተደርጓል ነው ያሉት። በተጨማሪም ከ3 ሚሊዮን ሊትር በላይ የምግብ ዘይት፣ ከ25 ሚሊዮን በላይ እንቁላል እና ከ34 ሚሊዮን ሊትር በላይ የወተት ምርት ለገበያ ማቅረብ መቻሉን አመልክተዋል። በዓሉን አስመልክቶ በሁሉም ምርቶች ላይ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የክትትልና ቁጥጥር ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አስታውቀዋል። በሌላ በኩል የክልሉ ህብረት ሥራ ኮሚሽን የግብይት ትስስር ባለሙያ አቶ ፈንታሁን ወርቅዬ፤ የግብርናና የፍጆታ ምርቶች በዩኒየኖች፣ በሸማቾች ህብረት ሥራ ማህበራት እና በሁለተኛ ደረጃ የገበያ ማዕከላት በኩል እየቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል። ለበዓሉ ከ16 ሺህ ኩንታል በላይ ሽንኩርትና ጤፍ፣ 4 ሺህ 500 ኩንታል የዳቦ ዱቄት፣ ከአንድ ሚሊዮን ሊትር በላይ የምግብ ዘይት፣ እንቁላልና የወተት ተዋጽኦዎች ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል። በሁሉም ዘርፍ በቂ የምርት አቅርቦት በመኖሩ በተረጋጋ ሁኔታ የበዓል ገበያ ግብይት እየፈጸሙ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዋ ወይዘሮ ስለናት ይዘንጋው ናቸው። የዋጋ ንረትን ለመቋቋም መንግስት በየአካባቢው የጀመረውን የ2ኛ ደረጃ የገበያ ማዕከላትን የማስፋፋት ስራ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።