ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በክልሉ የገጠሩን ማኅበረሰብ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Sep 20, 2026 113
ጨና/ሺሾንዴ/ ፤ መስከረም 10/2019 (ኢዜአ):- በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የገጠሩን ማኅበረሰብ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በክልሉ ካፋ ዞን ጨና እና ሺሾንዴ ወረዳዎች የተገነቡ ሁለት ሞዴል የገጠር መንደሮች ተመርቀው ለነዋሪዎች ተላልፈዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት የመደመር መንግስት የዜጎችን ሕይወት በተጨባጭ ወደ ተሻለ ደረጃ የሚቀይሩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። የክልሉ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ልማትን በማፋጠን የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የገጠር ሞዴል መንደሮች መገንባታቸውን አንስተዋል። በወረዳዎቹ የተገነቡት እነዚህ ሞዴል መንደሮች የሌማት ትሩፋት ፓኬጆችንና መሰረተልማት ያሟሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በሌላ በኩል የቤት እንስሳት እና የሰው መኖሪያ ለየብቻ መገንባቱ የማኅበረሰቡን ጤና በማስጠበቅ በኩል ከፍተኛ ሚና አለው ነው ያሉት። የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ በበኩላቸው፤ በመደመር እሳቤ በገጠር የሚገኙ ዜጎች የተሻለ ሕይወት መምራት የሚችሉበትን ምቹ ሁኔታ መፍጠር እየተቻለ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ 3 ሞዴል የገጠር መንደሮች መገንባታቸውን ጠቅሰው በሞዴል መንደሮቹ የተካተቱ የልማት ሥራዎችን በማጠናከር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡ የጨና ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ታምራት ካሳ፤ መንግሥት በሰው ተኮር ተግባራት ሁሉንም ፍትኃዊ በሆነ መንገድ ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው በወረዳው የተመረቀው የኮዳ ሞዴል የገጠር መንደር የማህበረሰቡን የአኗኗር ዘይቤ የሚያዘምን መሆኑን ነው የጠቆሙት፡፡ የገጠር ሞዴል መንደሩ አርሶ አደሮችን ወደ ዘመናዊ የአኗኗር ሥርዓት እያሸጋገረ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የሺሾንዴ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ደምሴ ገብረ ማርያም ናቸው። በወረዳው ዳሔራ ቀበሌ የተገነባው ሞዴል የገጠር መንደር መሰረተ ልማትና የቤት ቁሳቁስ የተሟላለት መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ፍትሃዊ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የህልውና እና የቀጣናዊ ደህንነት የማረጋገጥ መሠረት ነው
Sep 20, 2026 125
አዲስ አበባ፤ መስከረም 10/2019 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያ ፍትሃዊ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የብሄራዊ ጥቅም፣ የህልውና፣ የቀጣናዊ ደህንነት የማረጋገጥና ኢኮኖሚያዊ ትስስር የማጠናከር መሠረት ነው ሲሉ ምሁራን ገለጹ። የባህር በር ባለቤት የነበረችው ኢትዮጵያ፣ በሴራ ያጣችው ይህ ተፈጥሯዊ ሀብቷ አሁን ካለው የህዝብ ቁጥርና ፈጣን ኢኮኖሚያዊ ዕድገቷ አኳያ የህልውና ጉዳይ ሆኗል። አሁን ላይ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የኢትዮጵያውያን ጥያቄ ብቻ ሳይሆን፣ የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ሰፊ ድጋፍ እያገኘ መጥቷል። ይህ የፍትህና የልማት ጥያቄ የሰላም እና የኢኮኖሚ ትስስር በሚያጠናክር መልኩ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እውን እንዲሆን መንግስት ያላሰለሰ ጥረት ማድረጉን ቀጥሏል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌዴራሊዝምና ገቨርናንስ መምህርና ተመራማሪ ተስፋዬ ጂማ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ የቀይ ባህር ጉዳይ ለኢትዮጵያ ከንግድና ገቢ ምንጭነት የዘለለ የሉዓላዊነትና የህልውና ጉዳይ ነው። የባህር በር ማግኘት ሀገሪቱ የንግድ ልውውጧን ከማስፋፋት ባለፈ የግብርናና የዓሣ ሀብት ልማቷን ለማሳደግ ወሳኝ ሚና አለው። በተጨማሪም ይህ እጅግ አስፈላጊ የጂኦፖለቲካዊ ዕድል በቀጣናውና በዓለም አቀፍ መድረክ የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊና ፖለቲካዊ ተጽዕኖ በከፍተኛ ደረጃ ያጠናክረዋል። በመሆኑም የቀይ ባህር ተደራሽነት ለሀገሪቷ ሁለገብ ደህንነትና ቀጣይ እድገት ዋስትና የሚሰጥ መሠረታዊ ጉዳይ መሆኑ አንስተዋል። የአዲስ አበባ አመራር አካዳሚ መሪ ተመራማሪ አቶ ሰለሞን ተፈራ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያን የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በትክክል ለመረዳት የታሪካዊ፣ ህጋዊ እና የጂኦፖለቲካ ዳራዎችን መመርመር ይገባል ብለዋል። እጅግ ተለዋዋጭ በሆነው የቀጣናው የፀጥታና የፖለቲካ ቁመና ውስጥ የባህር በር ባለቤት መሆን ለኢትዮጵያ የህልውናና የሉዓላዊነት ወሳኝ ጉዳይ መሆኑም ጠቁመዋል። ስለሆነም ምሁራን ለዚህ ሀገራዊ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ አጋዥና አዋጭ ሃሳቦችን በማቅረብ ታሪካዊ ሀላፊነታቸውን መወጣት እንደሚችሉ አስገዝበዋል። የኢትዮጵያን የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከሀገራዊ ጥቅም እና ከህልውናዋ ጋር አያይዞ ማየት እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል። የሀገሪቷ እያደገ የመጣው ህዝብ ቁጥርና ተለዋዋጭ የጂኦ ፖለቲካ ሁኔታ ጉዳዩን የበለጠ ወሳኝ እንደሚያደርገው ገልጸዋል። ለዚህም ምሁራን በጥናትና ምርምር የተደገፈ መረጃ በማመንጨት የሀገሪቱን ጥቅም በዓለም አቀፍ መድረኮች በማንሳት እና በማስገንዘብ ለሀገራቸው ብሔራዊ ጥቅም መከበረ አዎንታዊ ሚና ማበርከት እንደሚችሉ ተናግረዋል። የዓባይ እና የቀይ ባህር ስትራቴጂክ ፎረም ሰብሳቢ አበበ ገመቹ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ የኢትዮጵያን የባህር ባለቤትነት ጥያቄ ጉዳይ ምሁራን በአንድ ተቋም ተሰባስበው በጥናትና ምርምር፣ የፖሊሲ ሀሳቦችን በማመንጨት በአህጉራዊና ዓለም አቀፍ መድረኮች ሊያሰሙ ይገባል። የዓባይ እና የቀይ ባህር ስትራቴጂክ ፎረም ይህንን ዓላማ ለማሳካት የተቋቋመ ስትራቴጂክ ፎረም መሆኑን ጠቅሰው፣ ከጂኦግራፊ፣ ከህዝብ ብዛት፣ ከፍትሃዊነትና ከቀጣናዊ ትስስር አኳያ ጥናቶችን በማካሄድ የሀገሪቱን ጥቅም የሚያስከብሩ ሀሳቦችን እያመነጨ እንደሚገኝ አብራርተዋል። የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ጉዳይን ኢትዮጵያ በያዘችው የሰላማዊ ዲፕሎማሲ መንገድ በመቀጠል የባህር ጥያቄዋን በጽኑ ማራመድ መቻሏ የሚደነቅ መሆኑንም ገልጸዋል።
በክልሉ በኮንስትራክሽን ዘርፍ የተሰማሩ ተቋራጮች ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት በመጨረስ እድገቱን ማፋጠን አለባቸው
Sep 19, 2026 166
ባህር ዳር፤ መስከረም 9/2019 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በኮንስትራክሽን ዘርፍ የተሰማሩ ተቋራጮች ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት በመጨረስ ሁለንተናዊ እድገቱን በማፋጠን የበኩላቸውን መወጣት እንዳለባቸው ተጠቆመ። የአማራ ክልል ኮንስትራክሽን ስራ ተቋራጮች ማህበር 3ኛ መደበኛ ጉባኤውን በባህር ዳር ከተማ እያካሄደ ነው። በምክትል ርእሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ከተሞች ክላስተር አስተባባሪ አሕመዲን መሀመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ የመደመር መንግሥት ፕሮጀክቶችን ፈጥኖ በመጀመርና በጥራት በመጨረስ ጠንካራ እሴቶችን ገንብቷል። በዚህም ከተለመደው አካሄድ በመውጣት በፈጠራ፣ በፍጥነት፣ በጥራትና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ አሰራርን ተግባራዊ ማድረጉን አስረድተዋል። የኮንስትራክሽን ዘርፉ ከነበረበት የዘመናት ውድቀት በማንሰራራት የክልሉ የአምስት ዓመት ስትራቴጂና የ25 ዓመቱ የአሻጋሪና የእድገት ፍኖተ ካርታ ግብን ለማሳካት የሚያስችል አቅም እየተፈጠረ መምጣቱን ተናግረዋል። ፕሮጀክቶችን በፍጥነትና በጥራት በመጨረስ ለሀገር እድገትና ለህዝብ ተጠቃሚነት ለማዋል በዘርፉ የተሰማሩ ተቋራጮች ትልቅ ሚና እንዳላቸው አረጋግጠዋል። በፕሮጀክት አስተዳደር ላይ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን በመሙላት ክልሉንም ሆነ ሀገርን በትክክለኛው የእድገት አቅጣጫ እንድትጓዝ መንግሥትና ተቋራጮች በጋራ መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል። የኮንስትራክሽን ማህበር አባላቱ አቅም ካላቸው የሀገር ውስጥና የአለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር ትስስር በመፍጠር መንግሥትና ህዝብ የጣለባቸውን ሚና እንዲወጡም አስፈላጊው እገዛ እንደሚደረግ አስገንዝበዋል። የአማራ ክልል የኮንስትራክሽን ስራ ተቋራጮች ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ ሙሉቀን ቢተው በበኩለቸው ማሕበሩ ፍትሃዊ የስራ ውድድር እንዲሰፍን እና ህጋዊና ስርዓት ያለው ግብይት እንዲተገበርና የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። ማህበሩ የስነ- ምግባር ችግሮችን በማረም ዘርፉ ለሀገሪቱ እድገት ያለውን ከፍተኛ ሚና እንዲወጣ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት መስራቱን እንደሚቀጥል ነው የገለጹት።
በአማራ ክልል የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በተለያዩ መስኮች ኢንቨስት የሚያደርጉ ባለሀብቶች ቁጥር እየጨመረ ነው
Sep 19, 2026 135
ባህርዳር፤ መስከረም 9/2019 (ኢዜአ)፦ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በክልሉ በተለያዩ መስኮች ኢንቨስት የሚያደርጉ ባለሀብቶች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን የአማራ ክልል የኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ እንድሪስ አብዱ ገለጹ። የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ እና ሌሎችም የስራ ኃላፊዎች በባሕር ዳር ከተማ የሚገኙ የተለያዩ የኢንዱስትሪ ልማት እንቅስቃሴዎችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ወቅት ማብራሪያ የሰጡት የአማራ ክልል የኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ እንድሪስ አብዱ፤ በክልሉ የተፈጠረው አስቻይ ሁኔታ የኢንቨስተሮችን ተሳትፎ እያጠናከረ መምጣቱን ገልጸዋል። በ2018 በጀት ዓመት ብቻ ከ553 ቢሊዮን ብር በላይ ሀብት ያስመዘገቡ በክልሉ የተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ለመሰማራት መግባታቸውን ጠቁመዋል። በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ ያሉ ማነቆዎችን በመፍታት ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠር መቻሉ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ አስችሏል ያሉት ኃላፊው በዚህም ተጨባጭ ውጤት መገኘቱን ተናግረዋል። በዚህም የክልሉ የአምራች ኢንዱስትሪ ምርታማነት እና የኢንዱስትሪ ዘርፍ እድገት እያሳየ የመጣ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ኢንቨስት የሚያደርጉ የውጭና የሀገር ውስጥ ባለሀብቶች ቁጥር እየጨመረ ስለመምጣቱም ጠቁመዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም በዘርፉ የሚሰማሩ ኢንቨስተሮችን የመሳብ፣ የዘርፉን እድገትና ምርታማነትን የማስቀጠል ስራ ትኩረት የተሰጠው መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ ርእሰ መሥተዳድር ጉብኝትም ዋነኛ ዓላማ የኢንዱስትሪዎችን የስራ እንቅስቃሴ በመመልከት ለማበረታታት እና ለችግሮችም የመፍትሄ አቅጣጫ ለማመላከት መሆኑን ገልጸው በዚሁ መሰረት ቀጣይነት ያለው ስራ ይከናወናል ብለዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአርሶ አደሩ በመስኖ የማልማት አቅም እየተገነባ ነው
Sep 19, 2026 232
ጂንካ፤ መስከረም 9/2019 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አርሶ አደሩን ከዝናብ በተጨማሪ በመስኖ ዓመቱን ሙሉ የማምረት አቅም እየተገነባ መሆኑን የክልሉ መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ገለጸ። በክልሉ በአሪ ዞን ሰሜን አሪ ወረዳ ከ58 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ለመስኖ አገልግሎት የተጠለፈው ''የሳላ'' ወንዝ ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል። የመስኖ ፕሮጀክቱ ከ80 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከሁለት መቶ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ያደርጋል። በወቅቱም የቢሮው ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር እንዳሉት፣ የአካባቢውን አርሶ አደሮች ከክረምት ዝናብ በተጨማሪ በበጋ መስኖ ለማልማት የሚያስችላቸው ዕድል ተፈጥሯል። የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እና የኢኮኖሚ አቅሙን ለማሳደግ የመስኖ አውታሮችን የማስፋፋት ሥራ የክልሉ መንግሥት በትኩረት እየሠራ መሆኑን አንስተዋል። በሣላ ወንዝ የተሠራው አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክት አርሶ አደሩን ከክረምት ዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ የሚደረገው ጥረት አካል መሆኑን ገልጸው በዚህም የአርሶ አደሩን በመስኖ የማልማት አቅም እየተገነባ መሆኑን አስረድተዋል። ለአገልግሎት ክፍት የሆነው የመስኖ ፕሮጀክት የአካባቢው አርሶ አደሮች በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥና የገቢ አቅማቸውን ለማሳደግ እንደሚረዳ ተናግረዋል። የሣላ የመስኖ ፕሮጀክት በሥርዓተ ምግብ ማጠናከሪያ ፕሮግራም የተገነባ ሲሆን፣ ከ80 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከሁለት መቶ በላይ አርሶ አደሮችና ቤተሰቦቻቸውን በቀጥታ ተጠቃሚ ያደርጋል ነው ያሉት። የሰሜን አሪ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ጎሳዬ ጉሳሬ በበኩላቸው፣ በወረዳው የሳላ ወንዝ መስኖ ፕሮጀክትን ጨምሮ ሌሎች የመስኖ ልማት ስራዎችን በማዘመንና ምርትና ምርታማነትን በመጨመር የአርሶ አደሩ ሕይወት እየተለወጠ ነው ብለዋል። የአሪ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ተወካይ አቶ አፌዶ ወርቁ በበኩላቸው፣ መንግሥት የአርሶና የአርብቶ አደሩን ሕይወት በዘላቂነት ለመለወጥ እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል። አርሶ አደሮቹ መንግሥት በፈጠረላቸው ዕድል በመጠቀም ኑሯቸውን ለመለወጥ መትጋት እንዳለባቸው አሳስበው፤ የመስኖ አውታሩ በደለል እንዳይሞላ መጠበቅና መንከባከብ እንዳለባቸውም አመልክተዋል። ከአካባቢው አርሶ አደሮች መካከል አቶ ንጋቱ ፀጋዬ እና አቶ ፌታ ጊዲፎ፣ የሳላ ወንዝ መስኖ ፕሮጀክት ለአርሶ አደሩ ዓመቱን ሙሉ በምርት ሥራ ላይ ተሰማርተው እንዲቆዩ ትልቅ ዕድልን እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል። ቀደም ሲል የግብርና ሥራዎቻቸው በዝናብ ላይ ብቻ ጥገኛ በመሆኑ ውስን ሰብሎችን ብቻ በማልማት ከእጅ ወደ አፍ የሆነ ኑሮ ይመሩ እንደነበር ጠቅሰው፣ አሁን በአካባቢው ለመስኖ አገልግሎት የሚውል ወንዝ በመጠለፉ ዓመቱን ሙሉ ማልማት የሚችሉበት አቅም መፈጠሩን ገልጸዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልሉ እና የአሪ ዞን የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የአካባቢው የሀገር ሽማግሌዎች እና ተጋባዥ እንግዶች ታድመዋል።
በአማራ ክልል ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ የልማት ጥያቄዎችን ለመመለሰ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Sep 19, 2026 128
ደሴ፤ መስከረም 9/2019(ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል ኢኮኖሚው በሚያመነጨው ልክ ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ በቅንጅት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ ። የደሴ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች መምሪያ የገቢ አሰባሰብ አቅሙን በማሳደግ ህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል የምክክር መድረክ ከባለድርሻ አካላት ጋር አካሂዷል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ገቢዎች ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ፍቅረማሪያም ደጀኔ እንደገለጹት፤ የህብረተሰቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ የገቢ አቅምን አሟጦ ለመጠቀም የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በተለይም ክልሉ የሚያመነጨውን ገቢ በሚፈለገው ልክ በመሰብሰብ ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሰፋፊ የልማት ሥራዎችን ለማከናወን ግብ ተይዞ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የገቢ አሰባሰብ ስርዓቱን ዲጂታል በማድረግና አዳዲስ አሰራሮችን በመከተል በተያዘው በጀት ዓመት ከ166 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን ነው የጠቆሙት። እስካሁን በተደረገው ጥረት ከ18 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉንም አስታውቀዋል። ይህም ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ6 ቢሊዮን ብር ብልጫ ያለው ሲሆን፤ በክልሉ እያደገ የመጣውን ገቢ የመሰብሰብ አቅም በማስቀጠል የተሻሉ ሥራዎችን ለማከናወን መታቀዱንም አክለው ገልጸዋል። በክልል ኢኮኖሚው የሚያመነጨው ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ህብረተሰቡ የሚያነሳችውን የልማት ጥያቄዎች በሚፈለገው ልክ ለመመለስ በቅንጅት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውንም አስረድተዋል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሞላልኝ በበኩላቸው፤ በተያዘው በጀት ዓመት ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ የተሻሉ ተግባራትን ለማከናወን ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል። በከተማዋ በበጀት ዓመቱ 8.2 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ የታቀደ ሲሆን፤ አዳዲስ አሰራሮችንና ቴክኖሎጂዎችን በመተግበር እቅዱን ለማሳካት ጥረት እንደሚደረግ ገልጸዋል። የደሴ ከተማ ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ መንግስቱ አበበ በበኩላቸው፤ በከተማዋ በበጀት ዓመቱ የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በተደረገ እንቅስቃሴም ከ719 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን አመልክተው፤ መምሪያው የገቢ አሰባሰብ አቅሙን በማሳደግ የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ ያላሰለሰ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በዚሁ የምክክር መድረክ ላይ የክልል፣ የከተማና የክፍለ ከተማ አመራሮች እንዲሁም የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
የእጣንና ሙጫ ደኖችን ለመንከባከብ የማህበረሰብ አቀፍ የደን ጥበቃ ሥራዎች እየተካሔደ ነው
Sep 19, 2026 109
ገንዳውኃ፣ መስከረም 9/2019 (ኢዜአ):- የእጣንና ሙጫ ደኖችን በመንከባከብ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ የማህበረሰብ አቀፍ የጥበቃ ሥራዎች እየተካሔደ መሆኑን የሰሜን ጎንደር ደንና አካባቢ ጥበቃ ተጠሪ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ፡፡ የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ወይዘሮ መልካም ዋሲሁን እንደገለጹት፣ የደን ሀብቱን በመንከባከብ፣ ዘመናዊ የእጣንና ሙጫ አመራረት መንገድን በመከተልና የምርት ጥራትን በመጠበቅ ለገበያ እንዲቀርብ እየተደረገ ይገኛል። በዋናነትም የእጣንና ሙጫ ደኖችን በመንከባከብና በማልማት ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እንዲቻል የማህበረሰብ አቀፍ የደን ጥበቃ ሥራዎች ላይ በማተኮር እየተሠራ ነው ብለዋል። በዚሁ መስክ ሥራ አጥ ወገኖችን በማደራጀት ሕገ-ወጥ የደን ጭፍጨፋንና የደን ውጤቶች ዝውውርን በማስቆም ከዘርፉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉንም ነው የተናገሩት። አምራቾችም ዘመናዊ የምርት አሰባሰብና የአያያዝ ዘዴዎችን በመከተል ጥራት ያለው የእጣንና ሙጫ ምርት ለማቅረብ እንዲችሉ እገዛና ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አስገንዝበዋል። በተጠናቀቀው የበጀት ዓመትም ከሰባት ሺሕ ኩንታል በላይ የእጣን ምርት ለገበያ በማቅረብ ከ374 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልጸዋል። ከተገኘው ገቢ ውስጥም 74 ነጥብ 9 ሚሊዮን ብር የሚሆነው መንግሥት ከሮያሊቲ ክፍያ ገቢ ያደረገው መሆኑን አስረድተዋል። በዞኑ የሌንጫ አዲስ ሕይወት ሕብረት ሥራ ማኅበር ሊቀመንበር አቶ በየነ ውቤ እንደገለጹት፣ እጣንና ሙጫ በማምረት ሥራ ላይ በማኅበር በመደራጀት ባለፈው ዓመት ወደ ማምረት ሥራ መግባታቸውን ይገልጻሉ። በተጠናቀቀው የበጀት ዓመትም ማኅበራቸው 362 ኩንታል የእጣንና ሙጫ አምርቶ ለገበያ በማቅረብ ከ21 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘቱን ገልጸዋል። ሌላው በመተማ ወረዳ በመሸሃ ቀበሌ በእጣን ምርት የተሰማሩት አቶ አየነው ሲሳይ፣ በተጠናቀቀው የ2018 ዓ.ም. ከአንድ ሺሕ ኩንታል በላይ እጣን ለገበያ ማቅረባቸውን ተናግረዋል። በተደጋጋሚ በሚሰጣቸው ሥልጠና አማካኝነት ደኑን ሳይጎዱ ጥራቱን የጠበቀ እጣን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ እንደሚገኙም አስገንዝበዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የስራ እድል ፈጠራ አማራጮችን ወደ ውጤት የመቀየር ተግባራት ይጠናከራሉ
Sep 18, 2026 326
ሆሳዕና ፤ መስከረም 8/2019 (ኢዜአ) ፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የስራ እድል ፈጠራ አማራጮችን ወደ ውጤት የመቀየር ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ስራ እድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡ የክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ኢንተርፕራይዞች ልማት ቢሮ ያለፈውን በጀት ዓመት አፈጻጸም እና የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ የሚመክር መድረክ በሆሳዕና ከተማ አካሄዷል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ልዩ አማካሪ ንጉሤ አስረስ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ አማራጮችን ወደ ውጤት በመቀየር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ተግባራት ይጠናከራሉ። በተለይም በዘርፉ የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የአሠራር እና የድጋፍ ማዕቀፎች መዘርጋታቸውን ጠቁመዋል። የሥራ ዕድል ፈጠራውን ለማበረታታትም ኢንተርፕራይዞችን በመደገፍ የተግባር ሥልጠና እንዲሰጡ መደረጉን ጠቅሰዋል። በዘርፉ የተመዘገቡ ስኬቶችን ለማጠናከር የባለድርሻ አካላት ርብርብ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል። የክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሙስጠፋ ኢሳ በበኩላቸው፤ በክልሉ በበጀት ዓመቱ የሥራ ዕድል ፈጠራን በማስፋፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። በዚህም በግብርና፣ በአገልግሎት እና በኢንዱስትሪው ዘርፍ ከ450 ሺህ በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ከ5 ሺህ 900 ሄክታር በላይ መሬት እና 600 የሚጠጉ ሼዶች ለኢንተርፕራይዞች ተዘጋጅተዋል ብለዋል። ከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ የብድር አቅርቦት መዘጋጀቱን እና ቀደም ባሉት ዓመታት ሼዶች ወስደው ሀብት ያፈሩ አንቀሳቃሾችን ለማሸጋገር ግብ ተይዞ ወደ ትግበራ ምዕራፍ መገባቱንም ኃላፊው ገልጸዋል። የስልጤ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራ እና ኢንተርፕራይዞች ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ አብዱራህማን ወርቅቾ፣ ዞኑ በሥራ ዕድል ፈጠራ ያሉ ጸጋዎችን ለይቶ በመጠቀም ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን ጠቁመዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ወጣቶችን በሥራ ዕድል ፈጠራው ተጠቃሚ ለማድረግ ከ1 ሺህ 350 ሄክታር በላይ መሬት እና ከ150 በላይ አዳዲስ ሼዶችን ገንብቶ ለማስረከብ ታቅዷል ብለዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳ እና የከተማ አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለ9ኛ ጊዜ የአፍሪካ ምርጡ አየር መንገድ በመባል ተሸለመ
Sep 18, 2026 559
አዲስ አበባ፤ መስከረም 8/2019 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በ2026 የስካይትራክስ የዓለም አየር መንገድ ሽልማት ለዘጠኝ ተከታታይ ዓመት በአፍሪካ ምርጡ አየር መንገድ በመባል ሽልማትን አግኝቷል። አየር መንገዱ በአፍሪካ ምርጥ የቢዝነስ ክላስ እና በአፍሪካ ምርጥ የኢኮኖሚ ክላስ አገልግሎት ሽልማቶችንም ተቀብሏል። የአፍሪካ ቀዳሚው አየር መንገድ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በ2026 የSKYTRAX የዓለም አየር መንገድ ሽልማቶች ላይ ለዘጠኝ ተከታታይ ዓመት በመመረጥ የአህጉሪቱ ቁጥር አንድ አየር መንገድነቱን አረጋግጧል። ከዚህ ታላቅ እውቅና በተጨማሪ አየር መንገዱ በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎችም ሽልማቶችን አግኝቷል። ሽልማቶቹም በአፍሪካ ውስጥ ምርጥ አየር መንገድ፣ በአፍሪካ ውስጥ ምርጥ የኢኮኖሚ ክላስ አገልግሎት አሰጣጥ እና በአፍሪካ ምርጥ የቢዝነስ ክላስ የሚሉት ናቸው፡፡ ሽልማቶቹ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለጥራት ያለውን የማይናወጥ ቁርጠኝነት እንዲሁም በዓለም ዙሪያ ያሉ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ደንበኞች በኢትዮጵያ አየር መንገድ ላይ ያላቸውን እምነትና ታማኝነት ያንፀባርቃሉ። ዕውቅናው አየር መንገዱ የላቀ አገልግሎት ለመስጠት፣ ልዩ የደንበኞችን እርካታ ለመጠበቅ እና በዓለም አቀፍ አውታረ መረቡ ውስጥ እንከን የለሽ የጉዞ ልምድ ለማቅረብ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያጎላ ነው። በተጨማሪም የአየር መንገዱን ሰራተኞች ያላሰለሰ ጥረት የሚያጎላ ሲሆን፣ በአፍሪካ ግንባር ቀደም የአቪዬሽን ቡድን መሆኑን ያረጋግጣል። ሽልማቶቹ አየር መንገዱ የአገልግሎቶች እና የአሠራሮች ደረጃ በመጠበቅ ረገድ ያለውን ቁርጠኛነት የሚያረጋግጥ መሆኑን የአየር መንገዱ መረጃ ያመላክታል፡፡
በቡና የወጭ ንግድ የተመዘገበውን አበረታች ስኬት በቅመማ ቅመም መድገም የሚያስችል የምርታማነት አቅም እየተፈጠረ ነው
Sep 18, 2026 120
አዲስ አበባ፤ መስከረም 8/2019 (ኢዜአ):-በቡና የወጭ ንግድ የተመዘገበውን አበረታች ስኬት በቅመማ ቅመም ዘርፍም መድገም የሚያስችል የምርታማነት አቅም እየተፈጠረ መሆኑን የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን አስታወቀ። የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፣ የቅመማ ቅመም ዘርፉን ስልታዊ በሆነ መንገድ ለማዘመን አጠቃላይ ጥረቶች መጀመራቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት ሮዝመሪ፣ ኮረሪማ፣ ጥቁር አዝሙድ እና ዝንጅብልን ጨምሮ 16 የተለያዩ የቅመማ ቅመም ዓይነቶች ለውጭ ገበያ እየቀረቡ ይገኛሉ። ባለፈው የበጀት ዓመት ብቻ ከዚህ ዘርፍ 17 ሚሊዮን ዶላር ገቢ የተገኘ ሲሆን፣ አሁን ላይ ይህንን አፈጻጸም ወደ 20 ሚሊዮን ዶላር ለማሳደግ ታቅዶ እየተሠራ ነው። ለእነዚህ 16 የቅመማ ቅመም ዓይነቶች የሚሆን ዘመናዊ የአመራረት፣ የጥራት አጠባበቅ እና የገበያ ሥርዓት ፓኬጆች ተዘጋጅተዋልም ብለዋል። እነዚህን አዳዲስ ፓኬጆች ወደ መሬት ለማውረድ የሚያስችሉ ዝርዝር መመሪያዎችም መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ተግባራዊነቱን ውጤታማ ለማድረግም በአርሶ አደሮች እና በግብርና ባለሙያዎች ላይ ያተኮረ ሥልጠና መሰጠቱን ጠቅሰዋል። በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመቀጠል የምርት ጥራት ወሳኝ በመሆኑ ጥብቅ የቁጥጥር ሥርዓቶች እየተዘረጋ ይገኛል ብለዋል። በዚህ ረገድም ከኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት ጋር በምርት ጥራት ቁጥጥር ዙሪያ በጋራ ለመሥራት የሚያስችል የትብብር ስምምነት መፈረሙን አስታውቀዋል። አሁን ላይ በዓመት የሚመረተው የቅመማ ቅመም መጠን 10 ሺህ ቶን የደረሰ ሲሆን፣ ይህንን ወደ 13 ሺህ ቶን ከፍ ለማድረግና መዳረሻ ገበያዎችን ለማስፋት ግብ ተይዞ እየተሠራ ነው ብለዋል። በድህረ ምርት ዙሪያ ለአርሶ አደሮች በፓኬጅ የተደገፉ ሥልጠናዎች ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑ የምርት ጥራትን ለማረጋገጥ ዓይነተኛ ሚና እንዳለውም ገልጸዋል። እነዚህ የተቀናጁ ጥረቶች የኢትዮጵያን የቅመማ ቅመም ምርቶች ተወዳዳሪነት በማሳደግ የሀገሪቱን የውጭ ምንዛሬ ገቢ ከፍ እንደሚያደርጉት ይጠበቃልም ነው ያሉት።
የሶማሌ ክልልን ሕዝብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ፕሮጀክቶች በብቃትና በጥራት እየተፈጸሙ ነው
Sep 18, 2026 306
አዲስ አበባ፤ መስከረም 8/2019 (ኢዜአ):- የሶማሌ ክልልን ሕዝብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ፕሮጀክቶች በብቃትና በጥራት እየተፈጸሙ መሆኑን የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር ገለጹ። አፈ ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር በፌዴሬሽን ምክር ቤትና ተጠሪ ተቋማት በሶማሌ ክልል ጎዴ ከተማ በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የተገነቡ መኖሪያ ቤቶችን ለተጠቃሚዎች አስረክበዋል። አፈ ጉባዔው በዚሁ ወቅት፤ ለአቅመ ደካሞች የተገነቡት የመኖሪያ ቤቶች ዜጎች የነበረባቸውን የቤት ችግር በመቅረፍ አስተማማኝ መጠለያ እንዲኖራቸው የሚያደርግ ነው ብለዋል። ፌዴሬሽን ምክር ቤትም በክልሉ ከአቅመ ደካማ ወገኖች የቤቶች ግንባታ በተጨማሪ ለተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ በማቅረብ ድጋፍ ማድረጉን ገልጸዋል። እንዲሁም በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር አካባቢን በመጠበቅ ለቀጣይ ትውልድ የሚጠቅም መሠረት በመጣል የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል። የሶማሌ ክልል በመደመር መንግሥት የአስተዳደር ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ የልማት ፕሮጀክቶች እውን የሚሆኑበት ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል። በዚህም የክልሉን ሕዝብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ በርካታ የልማት ፕሮጀክቶች ተገንብተው የሕዝብን የልማት ጥያቄ በመመለስ ለአገልግሎት መብቃታቸውን አስረድተዋል። ለአብነትም በማኅበራዊ ዘርፍ ከተከናወኑ ተግባራት መካከል የጤና ተቋማት ግንባታን በማስፋፋት ሕብረተሰቡ በአቅራቢያው የሕክምና አገልግሎት የሚያገኝበት ዕድል መፈጠሩን ጠቁመዋል። በተጨማሪም በመንገድ፣ በአየር ማረፊያ መሠረተ ልማቶችና በኢንቨስትመንት ፍሰት የሕዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ድሎች መመዝገባቸውን አብራርተዋል። የመደመር መንግሥት የልማት ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት ጀምሮ ማጠናቀቅ ዋነኛ መለያው መሆኑን በመጥቀስ፤ ይህም የክልሉን ሕዝብ ተጠቃሚነት እያሻሻለ መሆኑን አብራርተዋል። የሶማሌ ክልል ሕዝብ ለዘላቂ ልማትና ሰላም ያለው ቁርጠኝነት የሚደነቅ ነው ያሉት አፈ ጉባዔ አገኘሁ፤ በቀጣይም ቀጣይነት ያለው ሰላምና ልማት የማረጋገጥ ተግባር ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል። የፌዴሬሽን ምክር ቤትም ከተጠሪ ተቋማት ጋር በጋራ በመሆን ሕብረ ብሔራዊነትን በማጠናከር በልማት ሥራዎች ያለውን ተሳትፎ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
በአማራ ክልል ከ8 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ወደ ስራ ተገብቷል
Sep 18, 2026 127
ባህር ዳር ፤ መስከረም 8/2019 (ኢዜአ):- በአማራ ክልል የኢንተርፕራይዞችን ኢኮኖሚያዊ አቅም ለማሳደግ ከ8 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸው ምርትና አገልግሎቶች የገበያ ትስስር ለመፍጠር ወደ ስራ መገባቱን የክልሉ ስራና ስልጠና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የገበያ ልማትና ግብይት ዳይሬክተር አቶ ፍቅረማርያም የኔአባት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አገልግሎት ሰጪና አምራች የኢንተርፕራይዞች የመወዳደር አቅማቸውን ከፍ ለማድረግ የገበያ ትስስር የመፍጠር ስራ እየተሰራ ነው። በክልሉ የሚገኙ 41 ሺህ 644 ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች በውጭና በሀገር ውስጥ ገበያ እንዲኖራቸው ትስስር በመፍጠር ተጠቃሚ የማድረግ ስራ ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል። የገበያ ትስስሩ በሀገር ውስጥ በኢንተርፕራይዞች መካከል ፣ በመንግስት ተቋማትና የልማት ድርጅቶች እንዲሁም ከተለያዩ የግል ኩባንያዎች ጋር የሚደረግ እንደሆነም አመልክተዋል። በሀገር ውስጥ ለግብይት የሚቀርቡ ምርቶችም ጥራትና ብዛትን መሰረት ያደረጉ ሲሆን የማኑፋክቸሪንግ፣ የኮንስትራክሽን፣ የግብርና ምርት እና የአገልግሎት ዘርፍ ውጤቶች እንደሆኑም ገልፀዋል። በውጭ ሀገራት ደግሞ በሚፈጠር ትስስር የጌጣጌጥ፣ የጨርቃጨርቅና የቆዳ ውጤቶች፣ የግብርና ምርት እና ሌሎች እንደሚገኙበት አብራርተዋል። ባለፉት ሁለት ወራት በተደረገ ጥረትም በሀገር ውስጥ ለአምስት ሺህ 435 ኢንተርፕራይዞች ከ791 ሚሊዮን ብር በላይ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ተችሏል ነው ያሉት። በውጭ ሀገር ደግሞ ለ21 ኢንተርፕራይዞች 30 ሺህ 660 ዶላር የሚያወጡ ምርቶች የገበያ ትስስር በመፍጠር ውጤታማ ስራዎችን ለመስራት መቻሉን ገልፀዋል። የገበያ ትስስር ዕቅዱን ለማሳካትም በተቀናጀ አግባብ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የኢንተርፕራይዞችን የመወዳደር አቅም የሚያሳድግ እንደሆነ አስገንዝበዋል። በባህርዳር ከተማ የሚገኘው የንፁህ ጫማ ማምረቻ ኢንተርፕራይዝ ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ንፁህ ይርጋ ፤ የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ ጫማዎችን በማምረት ለገበያ እያቀረቡ ነው። በየጊዜው በሚዘጋጁ ባዛሮች የሚያመርቷቸውን ምርቶች ለሸማቹ ህብረተሰብ በማስተዋወቅ በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ገልጸዋል። የገበያ ትስስር ለመፍጠር የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ቢቀጥል ስራቸውን ለማስፋት እንደሚረዳቸው ነው ያመለከቱት። በክልሉ ባለፈው በጀት ዓመት በሀገር ውስጥ 9 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር፤ በውጭ ሀገር ደግሞ አንድ ነጥብ 3 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጡ ምርቶች ትስስር መፍጠር እንደተቻለም ከቢሮው የተገኘ መረጃ ያመለክታል።
ተናግሮ ማድረግ ፣ ቃል ገብቶ መፈጸም !
Sep 18, 2026 127
ተናግሮ ማድረግ ፣ ቃል ገብቶ መፈጸም ! የዘንድሮው የኢትዮጵያ አዲስ ዓመት ተራ የቀን መቁጠሪያ ለውጥ ብቻ አይደለም። ሀገራችን አዲስ ገጽ ገልጣ አዲስ ታሪክ ጽፋለች፤ መርጣለች፣ መክራለች፣ አሸንፋለች፣ አንሰራርታለችም። ፈተናዎች ወደ ታላቅ ዕድል ተቀይረዋል። በጸኑ እና ዝቅ ብለው በሠሩ ልጆቿ ጥረት የዘመናት የአዙሪት ጥላ ላይመለስ ተገፏል፤ ባለፉት ጥቂት የለውጥ ዓመታት ብቻ ለበርካታ አስርት ዓመታት ያላሳካናቸውን ድሎች ማሳካት ችለናል። ሩቅ የማለም፣ አቅዶ የመጀመር እና በፍጥነት የማጠናቀቅ አዲስ የሥራ ባህልም ገንብተናል። ይህ የሀገራችንና የመንግሥቷ ልዩ መገለጫ ሆኗል። ዛሬ በኢትዮጵያ ሰማይ ሥር የሚጨበጥ ብርሃን ፈንጥቋል። ከአፈሙዝ የሥልጣን ውርስ ተላቆ «ሀገረ መንግሥት በሕዝብ ካርድ ብቻ ይጽና» የሚል ድምፅ ከአጽናፍ አጽናፍ አስተጋብቷል። ሕዝባችን ቀን በፀሐይ፣ ሌት በውርጭ፣ ከሕመሙ ታግሎ፣ አትምረጥ ካለው ጋር ገጥሞ፣ የሚፈልገውን ነግሮናል። ሀገር አጽንቷል፣ ዴሞክራሲን መርጧል። በሀገራዊ የምክክር ማዕቀፍ የኅብረ-ብሔራዊቷ ሀገራችን ልጆች ተሰባስበው ስለ እናት ሀገራቸው በአንድ አዳራሽ መክረዋል፤ ዘክረዋል። ይበጃል ያሉትን በጎ ሐሳቦች በነፃነት አቅርበዋል። በአጭሩ በኢትዮጵያ ምድር በዘመኑ አርበኞች አዲስ ገድል ተፈጽሟል። ይህ እውነት የልጆቻችንን ተስፋ ያለመለመ፣ በዘመናት መካከል በኩራት የምንተርከው ወርቃማ ታሪካችን ነው። አንቆምም! ገና ብዙ ሥራ አለብን፤ እንፈጥናለን፣ መሰናክሎቻችንን ሁሉ በብሕላት እየዘለልን ወደ ሀገራችን መሻቶችና ሕልሞች በጽናት እንዘልቃለን። ታላቅ ሀገር አለችን፤ እየተማከርን እንገነባታለን፣ እየገነባንም እንማክራለን። ሁሉንም አሸናፊ ያደረገው አዲሱ መንገዳችን ይኸው ነው። መመካከር ።መመካከር ። መመካከር። ባለፉት የለውጥ ዓመታት የሕግ የበላይነት በጥብቅ ዲሲፕሊን ከተመራበት መንገድ ጎን ለጎን፣ መንግሥታችን ያጠፉ ልጆቹን በምሕረት አቅፏል፤ በርካታ የፖለቲካ እስረኞችን በይቅርታ ፈትቷል። ይህ ውሳኔ ብዙ ሀገራት የተመኙት፣ ኢትዮጵያ ግን ያሳካችው የበቀል አዙሪትን የሰበረ ታላቅ እርምጃ ነው። ውሳኔው ለሀገራችን ዘላቂ ጥቅም ሲባል የተከፈለ ውድ ዋጋ መሆኑን የመደመር መንግሥት ይገነዘባል። ይቅርታ የጽኑ ሀገረ-መንግሥት ዋነኛ ምሰሶ ነው፤ ውሳኔው ከሀገራዊ ምክክሩ ጋር ተጣጥሞ ብሔራዊ መግባባትን ያጠናክራል። የተፈቱት ወገኖቻችን ዕውቀታቸውን እና አቅማቸውን ለሀገር ግንባታ እንደሚያውሉ እናምናለን፤ ይህም ለነገዋ ኢትዮጵያ የማይናወጥ መሠረት ይጥላል። ከፖለቲካዊ እና ማኅበራዊ መግባባት ጎን ለጎን፣ በአንድ ሀገር ፖለቲካዊ መረጋጋት እየተሻሻለ የሚመጣው በሀገር ደረጃ ጠንካራ የኢኮኖሚ ስኬቶች ሲመዘገቡ እና ሕዝባዊ አመኔታ ሲገነባ ነው። ኢትዮጵያ ይህን አድርጋዋለች። ዛሬ ላይ በሀገራችን እየተመዘገበ ያለው አጠቃላይ የኢኮኖሚ ዕድገት በአፍሪካ ፈጣኑ እና መሠረቱ የሰፋ አስደናቂው እድገት ነው። ይህን እውነት ባንዳውም ባዳውም ሳይወድ በግዱ ይቀበለዋል። የመደመር መንግሥት ጉርሷን የማትለምን እና ክብሯን የጠበቀች ሉዓላዊት ሀገር ለመፍጠር በሁሉም መስክ ጥረት አድርጓል ።አበራታች ስኬቶች ተመዝግበዋል። ከለጋሽ እጅ ስንዴ የመጠበቅ ታሪካችን አብቅቶ በበጋ ስንዴ ራስን ከመቻል ያለፈ አዲስ ታሪክ ጽፈናል። በየዓመቱ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል የራሳችንን ክብረ ወሰን ደጋግመን አሻሽለናል፤ በአካባቢ ጥበቃም ለዓለም አቀፍ ትብብር አርአያ ሆነናል። ይህ ስኬት በሌላ ሀገር የተፈጸመ ቢሆን ምንኛ በተነገረ ነበር፤ ዳሩ ግን እኛ ድልን ደጋግመን ያጣጣምን የጀግኖች አባቶቻችን ልጆች ነን። ፈጽመነዋል። ርዕያችን ሩቅ ነው ፣ መንገዳችን መደመር ነው፣ ስንደመር አትርፈናል ፤ ስንሰባሰብ ጠንክረናል። በሌሎች ሀገራት የጸብ መንስኤ፣ የሀገር ዕዳ የሆኑትን ማዕድናት እኛ የሀገር ምንዳ ፣ የሀገር ተስፋ አድርገናል፤ በታዳሽ ኃይል ፕሮጀክቶቻችን ቀጣናውን አስተሳስረናል፤ የከተሞቻችን ገጽታ በዘመናዊ የኮሪደር ልማት ተለውጧል። የኮንፈረንስ ቱሪዝም ተስፋፍቷል ፤ አዳዲስ የቱሪዝም መዳረሻዎችን ገንበተናል። ነባር ቅርሶቻችንንም አቧራቸውን አራግፈን ወደ ነገ አሻግርናል ። ትውልድን አስበን የዲጂታል 2030 ስትራቴጂን ተግባራዊ እያደረግን ነው። የመንግሥት አሠራርንም ግልጽና ቀልጣፋ ለማድረግ መሠረት ተጥሏል ። ከሁሉም በላይ ሀገራችንን ከሚሽኮረመም የውጭ ፖሊሲ አላቀን ለብሔራዊ ጥቅማችን በጽናት ቆመናል ፤ በአለም መድረክ የሚገባንን ጠይቀናል። የምንገነባው ሀገረ-መንግሥት የመደመር እሳቤ ላይ የተመሠረተ ነው ፣ ትኩረቱም በጽኑ ተቋማት ግንባታ ላይ ነው። የፍትሕ፣ የፀጥታ እና የዴሞክራሲ ተቋሞቻችን ጠንካራ መሠረት ይዘዋል። ወገባችንን አጥብቀን ዝቅ ብለን በሠራነው ሥራ ቀና ብለን መሄድ ጀምረናል፣ ዛሬ ላይ ሀገር የሚሸከሙ፣ መጪውን ጊዜ የተለሙ እና ከሥርዓት መቀያየር የተሻገሩ ተቋማዊ አቅሞች ተፈጥረዋል። ባለፉት ጥቂት ዓመታት፣ የለውጡ መንግሥት ልዩ የሚያርገውን መገለጫን አስተዋውቋል፤ ፕሮጀክቶችን ይጀምራል፣ አጠናቆም ይመርቃል። ይህ በሕዝባችን አንደበት ተደጋግሞ የሚነገር እውነትኛ ምስክርነት ነው። የተዘጉ ኢንዱስትሪዎች ተከፍተዋል፤ ለዘመናት የኪሳራ ምሳሌ የሆኑ ተቋማት ወደ ትርፋማነት ተሸጋግረዋል ፤ በኢንቨስትመንት ፣በኤክስፖርት እና በተኪ ምርት እመርታዊ ለውጥ አሳክተናል። ከዚህም በላይ ታላቁን የህዳሴ ግድባችንን ባጠናቀቅንበት ማግስት በጉባ ከ30 ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚያወጡ እና የኢትዮጵያን መጻኢ ዕድል የሚወስኑ አዳዲስ ሜጋ ፕሮጀክቶችን ለሕባችን አብሰረነዋል ። የኢነርጂ ዋስትናን ለማረጋገጥ የኒውክሌር ማዕከል ለመገንባት አዲስ ውል ታስሮ ሥራ ተጀምሯል ፤ በሶማሌ ክልል የኢትዮጵያ ጸጋዎችን ገልጠናል። የተፈጥሮ ጋዝ ማጣሪያ ፕሮጀክቶች ቀን ከሌት እየተሰራ ይገኛል ። በዓመት 100 ሚሊዮን መንገደኞችን የሚያስተናግደው የቢሾፍቱ ኤርፖርት የአፍሪካ አቪዬሽን ዘውድ ደፍቶልን በሰማዩ ያነግሰናል። በዓመት ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚያድነው የማዳበሪያ ፋብሪካም የግብርና ምርታማነትን በማረጋገጥ ለገበሬዎቻችን እፎይታ ይሆናል ፤ ተስፋችን ብዙ ነው። የብዙዎችን ህይወት የሚቀይረው የ1.5 ሚሊዮን ቤቶች ልማት ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በትብብር ሥራው ተጀምሯል። እናሳካዋለን ! ተናግሮ ማድረግ ፣ ቃል ገብቶ መፈጸም በመደመር መንግሥት ለትውልድ የተጣሉ ጠንካራ መሠረቶች ናቸው። የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት መስከረም 8 /2019 ዓ.ም
የዓባይ ወንዝና የቀይ ባሕር ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን የማረጋገጥ ጉዳይ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም የማስከበር ማዕከላዊ አጀንዳዎች ናቸው
Sep 17, 2026 305
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 7/2019 (ኢዜአ)፦የዓባይ ወንዝ ፍትሐዊ የውሃ ሀብት ተጠቃሚነትና የባሕር በር ባለቤትነትን የማረጋገጥ ጉዳይ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም የማስከበር ማዕከላዊ ስትራቴጂክ አጀንዳዎች መሆናቸውን ምሁራን ገለጹ። የአዲስ አበባ አመራር አካዳሚ የዓባይ ወንዝና የባሕር በር ጉዳዮችን በተመለከተ የፓናል ውይይት አካሂዷል። የማኅበራዊ ሳይንስ ምሁሩ ብርሃኑ ሌንጂሶ (ዶ/ር) በፓናሉ ላይ እንዳሉት፣ የዓባይና የባሕር በር ጉዳዮች በጂኦፖለቲካዊና በልማታዊ ትስስራቸው ተነጣጥለው ሊታዩ አይገባም። የዓባይ ወንዝ ጉዳይ የልማት፣ የኢኮኖሚና የቀጣናዊ ትብብር ማዕከል በመሆኑ በጋራ ጥቅም ላይ የተመሠረተ አቀራረብ ሊከተል እንደሚገባ አመልክተዋል። ሁለቱን ስትራቴጂካዊ ጉዳዮች በተቀናጀ የሀገሪቱ የውጭ ጉዳይና የልማት ስትራቴጂ መሠረት መምራት እንደሚያስፈልግም አንስተዋል። በዚህም የዓባይ ወንዝ ፍትሐዊ የውሃ ሀብት ተጠቃሚነትና የባሕር በር ባለቤትነትን የማረጋገጥ ጉዳይ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም የማስከበር ማዕከላዊ ስትራቴጂክ አጀንዳዎች መሆናቸውን አስገንዝበዋል። የአዲስ አበባ አመራር አካዳሚ መሪ ተመራማሪ አቶ ሰለሞን ተፈራ በበኩላቸው፣ የባሕር በርና የዓባይ ጉዳዮች ተነጣጥለው ሳይሆን በአንድ ሀገራዊ ማዕቀፍ ውስጥ ተቀናጅተው ሊታዩ እንደሚገባ ጠቁመዋል። ጉዳዮቹ በምሁራን ጥናትና በጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ሊመሩ እንደሚገባም ተናግረዋል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌዴራሊዝምና ገቨርናንስ መምህርና ተመራማሪ ተስፋዬ ጂማ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የባሕር በር ጉዳይ ከሉዓላዊነት፣ ከኢኮኖሚ ዕድገትና ቀጣናዊ ሰላም የተቆራኘ የብሔራዊ ጥቅም ጉዳይ ነው ብለዋል። የሀገር ህልውናን፣ ደህንነትንና የዜጎችን ማኅበራዊ ልማት ከሚያሳድጉ ጉዳዮች አኳያ፣ የባሕር በርና የዓባይ ወንዝ ጉዳዮች በአንድ ማዕቀፍ ውስጥ ሊታዩ እንደሚገባ አንስተዋል። ምሁራን በጥናትና ምርምር የተደገፈ የፖሊሲ ግብዓት በማቅረብ፣ እንዲሁም የሕዝብ ግንዛቤን በማሳደግ፣ ሀገራዊ ጥቅምን ለማስጠበቅ በሚደረገው ሂደት አዎንታዊ ሚና ማበርከት እንደሚችሉም ተናግረዋል።
የጋምቤላ ክልል ከተሞችን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶች ይጠናከራሉ
Sep 17, 2026 239
ጋምቤላ ፤ መስከረም 7/2019 (ኢዜአ)፦ የጋምቤላ ክልል ከተሞችን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) ገለጹ። የክልሉ የከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸምና የአዲሱ በጀት ዓመት እቅድ ላይ ያዘጋጀውን የውይይት መድረክ ዛሬ አካሄዷል። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የክልሉ ከተሞችን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። ከተሞችን ለነዋሪዎችና ለኢንቨስትመንት ምቹ ለማድረግ የመሠረተ ልማት ማስፋፋት ላይ የተጀመረው ጥረት እንደሚጠናከርም ገልጸዋል። ለዚህም የኮሪደር ልማትን ጨምሮ የንጹህ መጠጥ ውሃ፣ የውስጥ ለውስጥ መንገድና ሌሎች የመሰረተ ልማት አውታሮችን ተደራሽ በማድረግ የህዝቡን የመሰረተ ልማት ጥያቄ ለመመለስ ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል። ህብረተሰቡ ለከተሞች የመሰረተ ልማት ግንባታ፣ ጽዳትና ውበት ስራዎች መሳካትም እያደረገ ያለውን ሁለንተናዊ ተሳትፎና የበጎ ፈቃድ አገልግሎት አጠናክሮ እንዲያስቀጥልም ጥሪ አቅርበዋል። በበጀት ዓመቱ የተያዙ ፕሮጀክቶች በተቀመጠላቸው የጊዜ ሰሌዳ ተጠናቀው ለሕዝብ አገልግሎት እንዲበቁም የክትትልና ድጋፍ ስራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። የመድረኩ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት በከተሞች የሚታዩ የመጠጥ ውሃ፣ የውስጥ ለውስጥ መንገድና የፍሳሽ ማስወገጃ መስመር ተግዳሮቶችን ለመፍታት በትኩረት መስራት እንደሚገባ ጠቁመዋል። በግምገማ መድረኩ ላይ ከክልል፣ ከዞን፣ ከወረዳዎችና ከከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ የስራ ኃላፊዎችን ጨምሮ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያ የቴምር ልማትን በማዘመን ተጨማሪ የኤክስፖርት አቅም እየገነባች ነው
Sep 17, 2026 394
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 7/2019 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የቴምር ልማትን በማዘመን ተጨማሪ የኤክስፖርት አቅም እየገነባች መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ፕሮፌሰር ዓሊ መሃመድ ገለጹ። የግብርና ሚኒስቴር በአፋር ክልል ሰመራ ከተማ ከመስከረም 10 እስከ 12 ቀን 2019 ዓ.ም የሚካሄደውን ሁለተኛውን ዓለም አቀፍ የቴምር ፌስቲቫል አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። ፌስቲቫሉ በአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ በግብርና ሚኒስቴር እና በኸሊፋ ኢንተርናሽናል አዋርድ ፎር ዴት ፓልም ኤንድ አግሪካልቸራል ኢኖቬሽን በጋራ ትብብር የሚዘጋጅ ነው። የግብርና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ፕሮፌሰር ዓሊ መሃመድ በመግለጫው እንዳሉት፣ ቴምር ለምግብነት፣ መድኃኒትነትና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ያለው ፋይዳ እጅግ ከፍተኛ ነው። መንግሥት ባህላዊና የተበታተነ አሰራር በማዘመን ምርቱን በሀገር ውስጥ ገበያ ብቻ ሳይገድብ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ከ500 ሺህ እስከ 600 ሺህ ሄክታር ለቴምር ልማት የሚሆን ምቹ መሬት ያላት ቢሆንም፣ እስካሁን የለማው መሬት መጠን 6 ሺህ ሄክታር ወይም 1.2 በመቶ ብቻ ነው ብለዋል። የቴምር ልማት እየተከሰተ ያለውን የአየር ንብረት ለውጥና የበረሃማነት መስፋፋት በብቃት የመቋቋም አቅም ያለው በመሆኑ ለአካባቢ ጥበቃም ሆነ ለኢኮኖሚ እድገት ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው አስገንዝበዋል። ይህን አቅም እውን ለማድረግ እንደ ተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ካሉ ሀገራት የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር በማድረግ ፈጣን ለውጥ ለማምጣት መታቀዱንም ተናግረዋል። ለዚህም የፌደራል መንግሥት፣ የአፋር ክልል፣ የዩኒቨርሲቲዎችና የምርምር ተቋማት ባለሙያዎች ተቀናጅተው የ10 ዓመት የምርምርና የልማት ፕሮግራም አዘጋጅተው ወደ ስራ መግባታቸውንም ገልጸዋል። የአፋር ክልል ግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ሃሩን ዓሊ በበኩላቸው፤ በክልሉ ከ250 ዓመታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረውን የቴምር ተክል ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ለማልማት ዕቅድ ተይዟል ብለዋል። በዚህም የተምር ምርታማነትን በዘመናዊ መንገድ በማሻሻል የምግብ ፍጆታንና የወጪ ንግድ አቅምን ለማጎልበት የአርሶ አደሩንና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሻሻል እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የኸሊፋ ዓለም አቀፍ የቴምርና የግብርና ፈጠራ ሽልማት ዋና ፀሐፊ ፕሮፌሰር አብደልወሃብ አልቡኻሪ ዘይድ በበኩላቸው፤ የቴምር ፌስቲቫሉ አርሶ አደሮችን፣ ተመራማሪዎችን፣ ሙያተኞችንና ውሳኔ ሰጪዎችን የሚያገናኝ ታሪካዊ መድረክ ነው ብለዋል። ይህ መድረክ በሀገሪቱ ያለውን ያልተነካ የቴምር አመራረት ዕድል ከማጎልበቱም በላይ በዘመናዊ አሠራሮች እና በወደፊት የአመራረት ዘዴዎች ላይ ያተኮረ ሳይንሳዊ ውይይት እንዲጀመር መንገድ መክፈቱን አብራርተዋል። በአፋር ክልል በሚካሄደው በዚህ የሦስት ቀናት ፌስቲቫል ላይ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት፣ አምራቾች፣ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር ባለሀብቶች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ይታደማሉ።
የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ማረጋገጥ ብሔራዊ ጥቅም የማስጠበቅና የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት ጉዳይ ነው
Sep 17, 2026 176
አዲስ አበባ፤ መስከረም 7/2019 (ኢዜአ):- የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ማስመለስ ብሔራዊ ጥቅምን የማስጠበቅ፣ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥና ቀጣናዊ ሰላምን የማጠናከር ጉዳይ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የወጣቶችና ስፖርት አማካሪ ሚኒስትር ቀጀላ መርዳሳ ገለጹ። የአዲስ አበባ አመራር አካዳሚ የዓባይ ወንዝና የባሕር በር ጉዳይን በተመለከተ የፓናል ውይይት እያካሄደ ይገኛል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የወጣቶችና ስፖርት አማካሪ ሚኒስትር ቀጀላ መርዳሳ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የባሕር በር ከኢትዮጵያ የኢኮኖሚ፣ የጸጥታ፣ የኃይል አቅርቦትና የንግድ ትስስር ጋር የተቆራኘ ነው። ቀይ ባሕር ከዓለም አቀፍ የንግድና የኃይል ማጓጓዣ መስመሮች ጋር የተሳሰረ መሆኑን ገልጸው፤ ለኢትዮጵያ የንግድ ተደራሽነት፣ የሎጂስቲክስ አቅም፣ የኢኮኖሚ ተወዳዳሪነትና ጸጥታ ወሳኝ ሚና አለው ብለዋል። ለኢትዮጵያ የባሕር በር ብሔራዊ ጥቅም የማስጠበቅ፣ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትና የቀጣናውን ሰላም የማረጋገጥ ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል አምባሳደር ዲና ሙፍቲ፤ የባሕር በር ከኢትዮጵያ ታሪክ፣ ጂኦግራፊ፣ ኢኮኖሚና የጸጥታ ሁኔታ ጋር የተያያዘ ዘላቂ ሀገራዊ አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከቀይ ባሕር ጋር ያላት የጂኦግራፊ ቅርበት፣ የሕዝብ ቁጥሯና እያደገ የመጣው ኢኮኖሚ የባሕር በር አስፈላጊነት የጎላ ያደርገዋል ብለዋል። ከሀገራዊ ጥቅም ባሻገር ከጎረቤትና ከቀሪው የአፍሪካ ሀገራት ብሎም ከዓለም አቀፍ ሥርዓት ጋር የሚኖረውን የኢኮኖሚና የጸጥታ ትስስር ማጤን እንደሚገባ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የባሕር በርን ጉዳይ በሰላማዊና በዲፕሎማሲያዊ መንገድ፣ በስምምነትና በትብብር መፍትሔ እንዲያገኝ አጥብቃ ትሻለች ብለዋል። የአዲስ አበባ አመራር አካዳሚ ፕሬዝዳንት ጣሰው ገብሬ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የባሕር በርና የዓባይ ጉዳዮች ከኢትዮጵያና ከአካባቢው የወደፊት የኢኮኖሚ፣ የደህንነትና የትስስር ጥቅሞች አንፃር ተመዝኖ መመራት እንዳለበት ገልጸዋል። የባሕር በርና የዓባይ ጉዳዮች በውይይት፣ በመተማመን፣ በሕጋዊ ማዕቀፎችና የሁሉንም ሕዝቦች ዘላቂ የጋራ ጥቅም ታሳቢ በማድረግ መመራት አለባቸው ብለዋል።
በክልሉ ያለውን የውሃ ሀብት ለመስኖ ልማት በመጠቀም ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር አሻደሊ ሀሰን
Sep 17, 2026 155
አሶሳ፤ መስከረም 7/2019 (ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ያለውን የውሃ ሀብት ለመስኖ ልማት በማዋል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ። የክልሉ ግብርና ቢሮ የ2019 ምርት ዘመን የመስኖ እርሻ ልማት ንቅናቄ መድረክ አካሂዷል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ የመስኖ ልማት ምርትና ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ ከተረጂነት ለመላቀቅ እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ቁልፍ ሚና እየተጫወተ ነው። በክልሉ የመስኖ ልማት ሥራ እየተሻሻለ መምጣቱን አመልክተው፤ አርሶ አደሩም ጥቅሙን በመረዳት ከመደበኛ የግብርና ሥራ ጎን ለጎን የመስኖ ልማት ሥራን በስፋት እየተገበረ ይገኛል ብለዋል። ከአርሶ አደሩ ባለፈ በእርሻ ኢንቨስትመንት የተሰማሩ ባለሀብቶች በመስኖ እርሻ ላይ ተሰማርተው የግብርና ዘርፉን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየሠሩ መሆኑን ገልጸዋል። ክልሉ ለመስኖ ልማት ምቹ የሆነ የውሃ ሀብት ያለው በመሆኑ አነስተኛ የመስኖ ግድቦችን በመገንባት የዘርፉን ልማት የማሳደግ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነው የጠቀሱት። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ባበክር ሀሊፋ በበኩላቸው፤ አርሶ አደሩ በመስኖ ልማት ስራ የሚያደርገው ተሳትፎ እየጨመረ መምጣቱ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ አስችሎታል ነው ያሉት። በተለይ በመስኖ የሚለሙ አትክልት እና ፍራፍሬዎችን ለኅብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ ገበያን የማረጋጋት ሥራ ለማከናወን መቻሉንም አንስተዋል። ባለፈው በጀት ዓመትም 57 ሺህ ሄክታር ማሳ በመስኖ በማልማት 14 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደተገኘ አመልክተው፤ በተያዘው በጀት ዓመትም 70 ሺህ ሄክታር ማሳን በመስኖ ለማልማት ወደ ሥራ መገባቱን አስታውቀዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ የዘርፉ አመራሮች እና ባለሙያዎች ተገኝተዋል።
የቱሪዝም ትንሳኤን ያበሰረው የመደመር እሳቤ
Sep 16, 2026 553
ኢትዮጵያ አስደማሚ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ የቱሪዝም ሀብቶች ባለቤት ናት ። የጎብኚዎችን ቀልብ የሚስቡ ደጋግመው ቢያዩዋቸው ፣ ቢታደሙባቸው የማይሰለቹ ተጠንተውም የማያልቁ ፀጋዎች ቢኖሯትም ለዘመናት በወጉ ሳትገልጣቸው የሚጠበቀውን ያክልም ሳይጎበኙ ሳይተዋወቁም ቆይተዋል። ይህን ባለማድረጓ ደግሞ ከዕልፍ የቱሪዝም ጸዋጋዎቿ ሳትቋደስ ዘመናትን ተሻግራለች። “በታሪክም ሆነ በተፈጥሮ ጸጋዎች ከኛ ጋር ሊወዳደሩ የማይችሉ ብዙ ሀገራት ከኢንዱስትሪው ብዙ አትርፈዋል። እኛ ግን እንቁዎቻችንን ደብቀን ታሪካችንን አቧራ አልብሰን ለዘመናት ቆይተናል።” የመደመር መንግሥት መጽሐፍ ገጽ 259 ዛሬ ግን ይህ ታሪክ እየተቀየረ ነው። ከመደመር መንግሥት አምስት ወሳኝ የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ በሆነው ቱሪዝም ቅርሶችንና ወሳኝ ፀጋዎችን ከቁስ ወደ ቁርስ እየለወጠ፣ ኢትዮጵያን እየገለጠ እንዲመጣ እየተደረገ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአራት ኪሎ ቤተመንግስት “ሀ” ተብሎ የተጀመረው አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻ ልማት በገበታ ፕሮጀክቶች አማካኝነት ወደ ሁሉም የሃገራችን ክፍሎች ተዳርሷል። በኢትዮጵያ ትኩረት ተነፍጓቸው የነበሩት የሀገራችን የቱሪዝም ሀብቶች በመደመር መንግሥት ቅድሚያ ተሰጥቷቸው ትንሳኤያቸው ተበስሯል። ለዘመናት አቧራ ለብሰው የኖሩ ዕንቁ የቱሪዝም ሀብቶች አቧሯቸው እየተራገፈ ነው። ከዳሎል እስከ ስሜን ተራሮች ማራኪ ተፈጥሯዊ መስህቦች ይበልጥ ለዓለም እየተዋወቁ ነው። አዳዲስ ተፈጥሯዊ ፀጋዎችም በቱሪዝም ልማት ኢኒሼቲቮች የመገለጥና የመታወቅ ዕድል አግኝተዋል። የመደመር እሳቤ የምናብ ከፍታና የመፈጸም ልክ አንዱ ጉልህ ማሳያ የቱሪዝሙ ዘርፍ ፕሮጀክቶች ናቸው። ከነዚህ ኢኒሼቲቮችም መካከል አንዱ ከቤተ መንግስት እደሳት ጀምሮ አዲስ አበባን እንደ ስሟ አዲስ ያደረጋት የገበታ ለሸገር ፕሮጀክት ነው። የገበታ ለሸገር ፕሮጀክት የቱሪዝም አብዮትን በመቀስቀስ የአንድነት ፓርክን፣ እንጦጦና ወዳጅነት ፓርክና ሌሎች ተያያዥ ፕሮጀክቶችን ዕውን አድርጓል። ዛሬ ላይ አዲስ አበባን አዲስ መልክ አጎናጽፎ፤ የነተቡ ሰፈሮች ወደ ውብ መልኮች ተቀይረው የሚሊዮኖች ጎብኚዎች መዳረሻ ሆነዋል። ከገበታ ለሸገር በመቀጠል የኢትዮጵያን አዳዲስ መልኮች የገለጠው ኢኒሸቲቭ ደግሞ የገበታ ለሀገር ፕሮጀክት ነው። ገበታ ለሀገር ከኦሮሚያ ክልል የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ወንጪን፣ ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ዳውሮና ኮንታን የሸፈነው ኮይሻን፣ከአማራ ክልል የጣናን ምዕራባዊ ዳርቻ የተንተራሰችውን ጎርጎራን ውብ አድርጓል። እነዚህ ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያን አይነተ ብዙ ታሪክ፣ ተፈጥሮንና ባህል በመግለጥ ለኢትዮጵያ ተጨማሪ ሞገስና ድምቀት ሆነዋል። ከገበታ ለሀገር ቀጥሎ ገቢራዊ የተደረገው የገበታ ለትውልድ ፕሮጀክት አድማሱ በሶማሌ ክልል ሸበሌ ሪዞርትን፣ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ የደንቢ ኢኮ ሎጅን፣ በአማራ ክልል የሐይቅ ሎጎ ሪዞርትን፣ በአፋር ክልል የኒዒን ሌ ፓልም ሎጅ እንዲሁም የአርባምንጭ ኮንፈረንስ ሪዞርትን እውን አድርጓል። ከገበታ ለሸገር እስከ ገበታ ለትውልድ ፕሮጀክቶች ባሻገር የመደመር መንግስት ታሪካዊ ቅርሶችን የመጠበቅ፣ እሴት ጨምሮ የመግለጥ አኩሪ ስራዎችንም አከናውኗል። ለዚህ ደግሞ ከብሔራዊ ቤተ መንግስት ጀምሮ ጥንታዊ አብያተ መንግስታት፣ ታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቅርሶች ተጠግነዋል። የባለፉት ጥቂት ዓመታት የቱሪዝም ዘርፍ ለውጦች የኢትዮጵያን ገጽታ ያስተዋወቁ፤ በየአካባቢው ተስፋና ልማትን የፈነጠቁ፣ ዘመን ተሻጋሪ ስራዎች ናቸው። እነዚህ ፕሮጀክቶች በኢትዮጵያ የዕድገትና የብልጽግና ታሪክ ውስጥ በደማቁ የሚጻፉ አንቀጾች ሆነው ለትውልድ የተኖሩ ዓሻራዎች ናቸው።
የኢትዮጵያና እስራኤል ትብብር ወደ ላቀ ምዕራፍ ተሸጋግሯል-አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር)
Sep 16, 2026 418
አዲስ አበባ፤መስከረም 6/2019 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያና እስራኤል ሁሉን አቀፍ ትብብር መጠናከር የሀገራቱን ግንኙነት ወደ ላቀ ምዕራፍ ማሸጋገሩን በእስራኤል የኢትዮጵያ አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ገለጹ። አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤የሁለቱ አገራት ግንኙነት ጥልቅ ታሪካዊ መሠረት ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ግንኙነቱ አሁን ላይ በመንግሥታት ትብብር፣በኢንቨስትመንት፣በቴክኖሎጂ እና በሰዎች አቅም ግንባታ ላይ የተመሠረተ ሁሉን አቀፍና ዘመናዊ አጋርነት ላይ መድረሱን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ እና እስራኤል ከጥንት ጀምሮ የነበራቸው ልዩ ታሪካዊ ግንኙነት ዛሬ ለደረሰበት ጠንካራ የሁለትዮሽ አጋርነት እንዳበቃቸው ተናግረዋል። በአዲስ አበባ የሚገኘው የእስራኤል ኤምባሲ የሁለቱን አገራት የረጅም ጊዜ ግንኙነት ለማጠናከርና ለማስፋት በተለያዩ ዘርፎች በስፋት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አስረድተዋል። የሁለቱ አገራት አበይት የትብብር መስኮች አንዱ የሆነው ግብርና፤ የእስራኤል ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ኩባንያዎችን በመገንባት ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂዎችንና ባለሙያዎችን ወደ ሀገር ውስጥ እንዲያስገቡ መልካም አጋጣሚን መፍጠሩን ነው ያነሱት። የእስራኤል ኩባንያዎች በፍራፍሬና በአትክልት ልማት ላይ የተሰማሩባቸውን በቢሾፍቱ አካባቢ የሚገኙ የግብርና ስራዎች በማሳያነት ጠቅሰዋል። በዘርፉ ያለው ትብብርና ኢንቨስትመንት ኢትዮጵያ አቮካዶን ጨምሮ የግብርና ምርቶቿን ወደ አውሮፓ እና እስያ ገበያዎች የምታቀርብበትን አቅም እንዲያድግ አስተዋጽኦ አድርጓል ብለዋል አምባሳደር አብርሃም። በተጨማሪም የኢትዮጵያ ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለውጭ ባለሀብቶች፣ እስራኤላውያንን ጨምሮ ምቹ ሁኔታዎችን እየፈጠረ መሆኑን አመልክተዋል። የውጭ ባለሀብቶችን በመሳብ ረገድ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው የገለጹት አምባሳደሩ፤ የተደረጉት ማሻሻያዎች ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ስራ ለመጀመር እና የኢንቨስትመንት ዕድሎችን ለመመልከት እያገዟቸው እንደሚገኙ ተናግረዋል። የማዕድን አቅምን ጨምሮ የኢትዮጵያ ተፈጥሮ ሀብቶች ተጨማሪ የእስራኤል ኢንቨስትመንቶችን መሳብ የሚያስችሉ መሆናቸውን ነው ያስረዱት። የእስራኤል ኩባንያዎች ወርቅን ጨምሮ በተለያዩ ማዕድናት ፍለጋና ማምረት ስራዎች ላይ ተሰማርተው እንደሚገኙ ጠቁመዋል። ጤና ሁለቱ አገራት ትብብራቸውን እያሰፉባቸው ካሉ ዘርፎች መካከል አንዱ መሆኑን የገለጹት አምባሳደሩ፤ የእስራኤል ሀኪሞች ከኢትዮጵያ የህክምና ባለሙያዎች ጋር በመቀናጀት የአቅም ግንባታን ጨምሮ በተለያዩ መርሃ ግብሮች ላይ በትብብር እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መስኮች፣በተለይም በሳይበር ደህንነት ዙሪያ ያለውን ትብብር አምባሳደሩ አንስተዋል። እስራኤል የሳይበር ደህንነት ተግዳሮቶችን በመቅረፍ ረገድ ያከማቸችውን ልምድ ለኢትዮጵያ ለማካፈል እንደምትሻም ተናግረዋል።