ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የግብርናና የምግብ ሥርዓትን ማጠናከር ለአፍሪካ ዘላቂ ልማት ወሳኝ ነው
Sep 9, 2026 154
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ)፦የግብርናና የምግብ ሥርዓትን ማጠናከር አፍሪካ የአየር ንብረት ጫናን በመቋቋም ዘላቂ ልማቷን እንድታሳድግ ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ። በአዲስ አበባ ከተማ ከጳጉሜን 2 እስከ 4 ቀን ሲካሄድ የቆየው አህጉራዊ ጉባኤ ፍጻሜውን አግኝቷል። በጉባኤው ወቅት በአፍሪካ የግብርናና የምግብ ሥርዓትን ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር በማጣጣም የሕዝቦችን የምግብ ዋስትና እና የኑሮ ጽናት ለማሻሻል የሚያስችሉ ዋና ዋና አቅጣጫዎች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል። በዚሁ መድረክ ከ30 በላይ የአፍሪካ ሀገራት የተወጣጡ ተሳታፊዎች የተገኙ ሲሆን የአህጉሪቱን የግብርናና የምግብ አጀንዳ በዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ውይይቶች የበለጠ ማስገንዘብና ውሳኔዎችንም ወደ ተግባር ማሸጋገር በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ መክረዋል። የአፍሪካ የምግብ ሉዓላዊነት ህብረት (Alliance for Food Sovereignty in Africa - AFSA) አስተባባሪ ዶክተር ሚሊዮን በላይ እንደገለጹት፤ አፍሪካ በግብርናና በምግብ ሥርዓት ያላትን የራሷን ልምድና መፍትሔ በማጠናከር በአህጉርና በዓለም አቀፍ መድረኮች የራሷን አጀንዳ በተግባር ማስፈጸም ይገባታል። አህጉሪቱ በዘርፉ ያላትን መልካም ተሞክሮ የበለጠ ማጉላት እንዳለባት ጠቁመው ለተቋቋሚ የምግብ ሥርዓት ግንባታ አግሮ-ኢኮሎጂን ማስፋፋት፣ የገበሬዎችን የዘር ሀብት መጠበቅና የገበሬዎችን ተሞክሮ ከሳይንስ ጋር በማጣመር የተሻለ የግብርና ልማት ማምጣት እንደሚገባ አስረድተዋል። በተጨማሪም የአፈርና የውሃ ሀብትን በአግባቡ መጠቀም፣ የአካባቢ የምግብ ገበያዎችን ማጠናከርና አፍሪካ የምግብ ፍላጎቷን በተቻለ መጠን በራሷ ምርትና ሀብት በመሸፈን የምግብ ሉዓላዊነቷን ማረጋገጥ እንደሚገባት ገልጸዋል። የምግብ ሥርዓቱ ቀጥተኛ ተዋናዮች ሀሳባቸው በውሳኔዎች ውስጥ እንዲንጸባረቅ የሚያስችል ተጨባጭ ተሳትፎ ሊኖራቸው እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ በዘር ሀብት ጥበቃ፣ በአግሮ-ኢኮሎጂና በምግብ ሉዓላዊነት ያላትን ልምድ በማጠናከር ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ ማካፈል እንደምትችል ጠቁመዋል፡፡ የአርሶ አደሮችን የዘር ሀብት መጠበቅና አሀጉራዊ ተሞክሮዎችን ከሳይንሳዊ እውቀት ጋር በማጣመር የተሻለ የግብርና ልማት ለማስመዝገብ መስራት እንደሚገባ አስረድተዋል።      
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከዕዳ ተላቆ ወደ ውጤታማ የትርፋማነት ምዕራፍ ተሸጋግሯል - ኢንጂነር አሸብር ባልቻ
Sep 9, 2026 122
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከነበረበት ዕዳ ተላቆ ወደ የትርፋማነት ምዕራፍ መሸጋገሩን የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ አስታወቁ። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አመራርና ሠራተኞቹ በተገኙበት የዘንድሮውን የ2018 በጀት ዓመት "ንጹህ ኢነርጂ ለተሻለ ሕይወት" በሚል መሪ ሐሳብ የተቋም ቀኑን አክብሯል።   ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ በዚህ ወቅት፤ ኤሌክትሪክ ኃይል ኢትዮጵያን የአፍሪካ የታዳሽ ኃይል ማዕከል የማድረግ ራዕይ የሚያሳካ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በ2018 በጀት ዓመት በርካታ የኃይል መሠረተ ልማት ፕሮጀክቶችን፣ የኦፕሬሽንና የጥገና ሥራዎችን በመሥራት ተቋማዊ የመፈጸም አቅምን ማላቅ መቻሉን አስታውቀዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ የአሰላና የአይሻ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች መጠናቀቅ ኃይል የማመንጨት አቅምን ወደ 9 ሺህ 730 ሜጋ ዋት በማሳደግ የ23 በመቶ ዕድገት እንዲመዘገብ ማስቻሉን ተናግረዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም ጠቅላላ የኃይል ምርት አቅም 35 ሺህ 671 ጊጋ ዋት በሰዓት በማድረስ የ124 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ገቢ ማግኘት እንደተቻለ አስረድተዋል። ከኃይል ሽያጭና ዳታ ማይኒንግ 475 ነጥብ 7 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ መገኘቱም የተቋሙን የገቢ አቅም ከባለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ64 በመቶ ዕድገት እንዲመዘገብ አስችሏል ብለዋል። በአጠቃላይ በበጀት ዓመቱ 39 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ በማስመዝገብ ተቋሙ ለመጀመሪያ ጊዜ ከዕዳ ወደ ትርፋማነት የተሸጋገረበትን ስኬታማ ዘመን እንዳሳለፈ ጠቅሰዋል። በዚህም የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ከነበረበት ዕዳ ተላቆ ወደ ውጤታማ የትርፋማነት ምዕራፍ መሸጋገሩን አብስረዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ላስመዘገበው ስኬትም የተቋሙ አመራር፣ ሠራተኞችና ባለድርሻ አካላት ሚና የላቀ መሆኑን በማንሣት ለዚህ ሁሉንም አመስግነዋል። ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም የሁሉም ዜጎች ኩራትና አሻራ ያረፈበት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ተጠናቆ በይፋ የተመረቀበት ታሪካዊ ዕለት መሆኑንም አስታውሰዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የተቋም ቀንም የሕዳሴን ታሪካዊ ፍጻሜ በመዘከር የላቀ አፈጻጸም ለነበራቸው አመራርና ሠራተኞች ዕውቅና ለመስጠት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም በየዓመቱ ጳጉሜን 4 የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የተቋም ቀን ሆኖ እንደሚከበር አስታውቀዋል።
የእስያ መሰረተ ልማት ኢንቨስትመንት ባንክ የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት ስራዎች ለመደገፍ ያለውን ቁርጠኝነት አረጋገጠ
Sep 9, 2026 87
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ):- የእስያ መሰረተ ልማት ኢንቨስትመንት ባንክ የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት አጀንዳዎች እንደሚደግፍ አስታወቀ። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ አዲሷን የእስያ መሠረተ ልማት ኢንቨስትመንት ባንክ (AIIB) ፕሬዝዳንት ዙ ጂያዪን ዛሬ በጽህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል። በውይይቱ ላይ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ጣሰው ተሳትፈዋል። የሁለቱ ወገኖች ውይይት ባንኩ በቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ላይ ሊኖረው የሚችለውን ተሳትፎ ጨምሮ በአበይት የኢትዮጵያ የልማት ትኩረቶች ላይ ያተኮረ ነው። ከዚህም ባሻገር በኢነርጂ ዘርፍ እና የአየር ንብረት ለውጥን በሚከላከሉ ፕሮጀክቶች ዙሪያ ያላቸውን አጋርነት ማሳደግ፣ በዝቅተኛ ወለድ የሚሰጡ የብድር አቅርቦቶችን ማመቻቸት እንዲሁም ከሌሎች ባለብዙ ወገን የልማት ባንኮች ጋር በቅንጅት መሥራት በሚቻልበት ሁኔታ ላይም መክረዋል። በውይይቱ ወቅት የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ለፕሬዝዳንት ዙ ጂያዪ የኢትዮጵያ ሪፎርም አጀንዳ አፈጻጸም እና እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ያሉ ግዙፍ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ረገድ የተመዘገቡ ስኬቶችን አስመልክቶ ገለጻ አድርገዋል። ሚኒስትሩ አክለውም ባንኩ ኢትዮጵያ ቅድሚያ የምትሰጣቸውን የልማት ትኩረቶች መደገፍ የሚችልባቸውን የፋይናንስ አማራጮች አቅርበዋል። ፕሬዝዳንት ዙ ጂያዪ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በቀጣናው የኃይል ትስስርን በማስፋት ረገድ እየተወጣች ያለውን ግንባር ቀደም ሚና አድንቀዋል። ባንኩ የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት አጀንዳ ለመደገፍ ያለውን ቁርጠኝነትም አረጋግጠዋል። ሁለቱ ወገኖች አጋርነታቸውን በማጎልበት፤ ዘላቂና አሳታፊ የመሰረተ ልማት ዕድገትን በጋራ እውን ለማድረግ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል። የእስያ መሠረተ ልማት ኢንቨስትመንት ባንክ (AIIB) ፕሬዝዳንት ዙ ጂያዪ በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ይፋዊ የስራ ጉብኝት እያደረጉ እንደሚገኝ የገንዘብ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እና ሀገራዊ ምክክር ጉባዔ የመቻልና የአንድነት ሕብራዊነት መገለጫዎች ናቸው
Sep 9, 2026 118
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ) ፦ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እና ሀገራዊ ምክክር ጉባዔ ኢትዮጵያውያን በትብብር ያሳኳቸው የመቻልና የአንድነት ሕብራዊነት መገለጫዎች መሆናቸውን የሰላም ሚኒስቴር ገለጸ። የሰላም ሚኒስትር ፅህፈት ቤት ሃላፊ መብራቱ ካሳ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በአንድነት ማሰሪያ የተጋመዱ ናቸው። ኢትዮጵያውያን የተጋመድን ነን ሲባል ከቃል ባለፈ በዓድዋ ጦርነትና በሌሎች ሀገራዊ ሉዓላዊነትን ለመዳፈር በተቃጡ ጥቃቶች ላይ በመተባበር በተግባር አሳይተናል ብለዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የጋራ የላብ፣ የደምና የውሃ ጠብታ ውጤት መሆኑን በመግለጽ፤ የኢትዮጵያውያን በጋራ መቻልን ያሳያል ብለዋል። ኢትዮጵያውያን ከማንኛውም አካል ተፅዕኖ ነጻ በመሆን ራሳቸውን በራሳቸው መለወጥ ማሳደግና ማበልጸግ እንደሚችሉ ያሳዩበት የሕብራዊነት መገለጫ ነው ሲሉም ተናግረዋል። በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ጉባዔ በህዝቦች መካከል የዘመናት ቁርሾ ሆነው የቆዩ ልዩነቶችን በምክክር መፍታት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያን የጋራ ችግራቸውን በራሳቸው አቅም በምክክር ለመፍታት ያሳዩት ቁርጠኝነት ለጠንካራ ሀገረ መንግሥት ግንባታ ያላቸውን ቀናኢነት ያሳያል ብለዋል። ሀገራዊ ምክክር ጉባዔው ኢትዮጵያ የራሷን ችግር በራሷ እየፈታች ያለች ሀገር መሆኗን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በተግባር ያረጋገጠ መሆኑንም ገልጸዋል።
በአማራ ክልል ለዘመን መለወጫ በዓል በቂ የእርድ እንስሳትና ሌሎች ምርቶች ቀርበዋል
Sep 9, 2026 100
ባህር ዳር ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ) ፦ በአማራ ክልል ለዘመን መለወጫ በዓል የእርድ እንስሳትና ሌሎች ምርቶችን በበቂ መጠን ለተጠቃሚው ማቅረብ መቻሉን የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ አትክልት አሳቤ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለዘመን መለወጫ በዓል በበቂ መጠን የእርድ እንስሳት፣ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች መቅረባቸውን ገልጸዋል። ምርቶቹን ከኢንዱስትሪዎች፣ ከግብርና አምራቾች፣ ከኢንተርፕራይዞች፣ ከህብረት ሥራ ማህበራት እንዲሁም ከእንስሳትና አሳ ሀብት ተቋማት ጋር በመቀናጀት በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል።   በተለይም በትላልቅ ከተሞች በተገነቡ 2ኛ ደረጃ የገበያ ማዕከላት፣ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን ለሸማቹ በቀጥታ እንዲቀርብ መደረጉንም አስረድተዋል። በበዓሉ ወቅት የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይኖር ቀደም ብሎ በቂ ዝግጅት በመደረጉ፣ ህብረተሰቡ በአቅራቢያው እንዲገበያይ መደረጉንም ነው ያብራሩት። እስካሁን ባለውም ከ700 ሺህ በላይ የደለቡ ዳልጋ ከብቶች፣ በጎችና ፍየሎች እንዲሁም ከሁለት ሚሊዮን በላይ የስጋ ዶሮዎች ለበዓል ገበያ እንዲቀርቡ ተደርጓል ነው ያሉት። በተጨማሪም ከ3 ሚሊዮን ሊትር በላይ የምግብ ዘይት፣ ከ25 ሚሊዮን በላይ እንቁላል እና ከ34 ሚሊዮን ሊትር በላይ የወተት ምርት ለገበያ ማቅረብ መቻሉን አመልክተዋል።   በዓሉን አስመልክቶ በሁሉም ምርቶች ላይ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የክትትልና ቁጥጥር ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አስታውቀዋል። በሌላ በኩል የክልሉ ህብረት ሥራ ኮሚሽን የግብይት ትስስር ባለሙያ አቶ ፈንታሁን ወርቅዬ፤ የግብርናና የፍጆታ ምርቶች በዩኒየኖች፣ በሸማቾች ህብረት ሥራ ማህበራት እና በሁለተኛ ደረጃ የገበያ ማዕከላት በኩል እየቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል። ለበዓሉ ከ16 ሺህ ኩንታል በላይ ሽንኩርትና ጤፍ፣ 4 ሺህ 500 ኩንታል የዳቦ ዱቄት፣ ከአንድ ሚሊዮን ሊትር በላይ የምግብ ዘይት፣ እንቁላልና የወተት ተዋጽኦዎች ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል።   በሁሉም ዘርፍ በቂ የምርት አቅርቦት በመኖሩ በተረጋጋ ሁኔታ የበዓል ገበያ ግብይት እየፈጸሙ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዋ ወይዘሮ ስለናት ይዘንጋው ናቸው። የዋጋ ንረትን ለመቋቋም መንግስት በየአካባቢው የጀመረውን የ2ኛ ደረጃ የገበያ ማዕከላትን የማስፋፋት ስራ አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።
በክልሉ ለዘመን መለወጫ በዓል የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይከሰት በቂ ዝግጅት ተደርጓል
Sep 9, 2026 106
ወላይታ ሶዶ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ) ፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ለዘመን መለወጫ በዓል የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይከሰት በቂ ዝግጅት መደረጉን የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ አስታወቀ። የአዲስ ዘመን መለወጫ የበዓል ገበያን አስመልክቶ ኢዜአ ያነጋገራቸው የቢሮው ኃላፊ ወይዘሮ ሰናይት ሰለሞን እንደገለጹት፤ ለበዓሉ የሚያስፈልጉ ምርቶች በበቂ ሁኔታ እንዲቀርቡ ተደርጓል። ከዘመን መለወጫ በዓል በተጨማሪ በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች የሚከበሩ ህዝባዊ በዓላት እንዳሉ አስታውሰው፣ ለበዓል ገበያ በምርት አቅርቦቱ የተደረገው ዝግጅት ይህንንም ታሳቢ ያደረገ ነው ብለዋል። ከምርት አቅርቦት በተጨማሪ በገበያው ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር ሕብረተሰቡንና የተለያዩ አካላትን ያሳተፈ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ በልዩ ትኩረትና በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።   ወይዘሮ ሰናይት እንዳሉት መደበኛ ገበያዎችን ጨምሮ በክልሉ ባሉ ከ105 በላይ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ምርቶች ለሸማቹ በቀጥታ የቀረቡ ሲሆን፣ የግብርና ምርቶችም የህብረተሰቡን አቅም ታሳቢ በማድረግ እንዲቀርቡ ተደርጓል፡፡ ከኢንተርፕራይዞች፣ ከክልሉ ዶሮ እርባታ ተቋምና ሌሎች አካላት ጋር በመነጋገር የዶሮና እንቁላል ምርት እንዲቀርብ መደረጉን የገለጹት ወይዘሮ ሰናይት፣ በበዓል ገበያ ከወትሮ የተሻለ አቅርቦት መኖሩንና የተረጋጋ ግብይት እየተካሔደ ይገኛል ብለዋል። እንደ ኃላፊዋ ገለጻ፣ በክልሉ የሚገኙ የሸማች ሕብረት ሥራ ማህበራት ዘይት፣ ስኳር፣ ዱቄትና መሰል የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያቀርቡ ተደርጓል።   በበዓል ገበያ ለጤና ጠንቅ የሆኑ ባዕድ ነገሮች የተቀላቀበት ምርትን ማቅረብ ጨምሮ ሀሰተኛ የገንዘብ ኖቶች ሊዘዋወሩ ስለሚችል ህብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግና አጠራጣሪ ነገር ሲገጥመውም ፈጥኖ ጥቆማ በመስጠት እንዲተባበር አስገንዝበዋል። የክልሉ ሕብረት ሥራ ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳሙኤል ፎላ በበኩላቸው፤ ለዘመን መለወጫ በዓል አስፈላጊ የግብርና እና የፋብሪካ ምርቶች በስፋት መቅረባቸውን ተናግረዋል።   በክልሉ ያሉ 78 ሸማች መሰረታዊ ሕብረት ሥራ ማህበራት እና 3 ዩኒየኖች ከ25 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጭ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች ግዢ ፈጽመው ለገበያ ማቅረባቸውን ተናግረዋል። በወላይታ ሶዶ ከተማ ነጋዴ የሆኑት አቶ አክሊሉ ጎዳና እንዳሉት፣ ከተለያዩ አካባቢዎች የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶችን በማስመጣት በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ እያቀረቡ ይገኛሉ።   ወይዘሮ ፀሐይነሽ ካይሳሞ በበኩላቸው፤ በበዓል ገበያው የተሻለ የምርት አቅርቦት መኖሩ የሚፈልጉትን ምርት በአቅማቸው ለመሸመት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል።   ምርቶችን በስፋት ከማቅረብ ባለፈ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር በቅንጅት እየተደረገ ያለው ቁጥጥርና ክትትል ተጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።
በመዲናዋ ለዘመን መለወጫ በዓል በቂ የግብርና ምርቶች ቀርበዋል
Sep 9, 2026 92
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ) ፦ለዘመን መለወጫ በዓል በቂ የግብርና ምርቶች አቅርቦት መዘጋጀቱን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአርሶ አደርና ከተማ ግብርና ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ ለመጪው የ2019 አዲስ ዓመት በዓል የሚቀርቡ የግብርና ምርቶች ጥራት እና ደህንነት ላይ የቁጥጥር ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም ኮሚሽኑ አስታውቋል፡፡ የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር ፀጋ ለማ (ዶ/ር) በሰጡት መግለጫ፤ ከነሐሴ 28 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በተለያዩ የገበያ ባዛሮችና ማዕከላት ስጋ፣ ዶሮ እና እንቁላል በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ከምርት ጥራትና ደህንነት አንጻር በከተማዋ በሚገኙ ሶስት የቄራ ድርጅቶች ውስጥ ከ40 በላይ ስጋ መርማሪ ሀኪሞች ተመድበው ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑንም ገልጸዋል። በተጨማሪም የስጋ ደህንነትን ለማረጋገጥ ለስጋ ማጓጓዣ ተሽከርካሪዎች ልዩ የጥራት ደረጃ ተዘጋጅቶ ስርጭቱ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በሌላ በኩል፣ የወተት ምርት ጥራትና ደህንነትን ከመጠበቅ እስከ ስርጭት ባሉ ሂደቶች ተገቢውን ቁጥጥር ማድረግ የሚያስችል የአቅም ግንባታ ስራዎች መሰራታቸውን እና የጥራት መፈተሻ መሳሪያዎች እየተሟሉ መሆናቸውን አስታውቀዋል። ሕብረተሰቡ በበዓል ወቅት በሚያከናውነው ግብይትና የቅርጫ እርድ ወቅት ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርግም ምክትል ኮሚሽነሩ አስገንዝበዋል።
በወልቂጤ ከተማ ለበዓል ገበያ የኢንዱስትሪና ግብርና ምርቶች እንዲሁም የእርድ እንስሳት በተለያዩ አማራጮች ቀርበዋል
Sep 9, 2026 87
ወልቂጤ ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ) ፦ ለአዲስ ዓመት የበዓል ገበያ የኢንዱስትሪና ግብርና ምርቶች እንዲሁም የእርድ እንስሳት በተለያዩ አማራጮች መቅረባቸውን በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የወልቂጤ ከተማ ንግድና ገበያ ልማት ፅ/ቤት አስታወቀ። በጳጉሜን ወር እለቶቹን በተለያዩ መርሃ ግብሮች ከማክበር በተጓዳኝ ኢትዮጵያዊያን አዲስ ዓመትን ለመቀበል በዝግጅት ላይ ይገኛሉ። በዚሁ መሰረትም የግብርና እና ኢንዱስትሪ ምርቶች፣ የእርድ እንስሳት፣ አልባሳትና ሌሎችንም በመሸመት አዲሱን ዓመት ለመቀበል እየተዘጋጁ ነው።   በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ወልቂጤ ከተማና አካባቢው የበዓል ግብይትና አቅርቦቱን በተመለከተ የኢዜአ ሪፖርተር ቅኝት በማድረግ የሚመለከታቸውን የስራ ሃላፊዎችና ሸማቾችን አነጋግሯል። የወልቂጤ ከተማ ንግድና ገበያ ልማት ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ ግርማ ንቅበሸዋ፤ ለበዓል የምርቶችና የእርድ እንስሳት አቅርቦት በበቂ ሆኔታ መኖሩን ገልጸዋል። ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እንዲሁም ከንግዱ ማህበረሰብ ጋር ቀደም ብሎ በቅርበት በመነጋገር ለበዓል ገበያ ዝግጅት መደረጉን አንስተው በዚህም በተመጣጣኝ ዋጋ በቂ አቅርቦት እንዲኖር ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የቅዳሜ እና እሁድ ገበያን ጨምሮ በተለያዩ የገበያ አማራጮች በብዛትና በተለያዩ አማራጮች መቅረቡን አንስተው ህገ ወጥ ግብይትና ያልተጋባ ዋጋ ጭማሬ እንዳይኖር ጥብቅ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል።   በኢትዮጵያ ንግድ ስራዎች ኮርፖሬሽን የወልቂጤ ቅርንጫፍ ተጠሪ ናትናኤል ደበበ፤ ከእርሻ አርሶ አደሮች በቀጥታ በሚያመጡት ምርት፤ ከፋብሪካ እና ከቅዳሜ እና እሁድ ገበያ ምርቶች በብዛትና በጥራት ለሸማቾች መቅረቡን ተናግረዋል። ለበዓል ሲሸምቱ ካገኘናቸው መካከል አቶ ጥበበ ታምሩ፣ ወይዘሮ አመለወርቅ ታደሰ እና ወይዘሮ ብርዝነሽ አረጋ፤ የበዓል ገበያ አቅርቦቱ ብዙ አማራጮች ያሉት በመሆኑ በተመጣጣኝ ዋጋ በመግዛት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በአዳማ ከተማ ለዘመን መለወጫ በዓል መሰረታዊ የፍጆታ እቃዎች በተመጣጣኝ ዋጋ ቀርበዋል
Sep 9, 2026 105
አዳማ ፤ ጳጉሜን 4/2018 (ኢዜአ) ፦ለዘመን መለወጫ በዓል የሚሆኑ መሰረታዊ የፍጆታ እቃዎች በተመጣጣኝ ዋጋና በበቂ ሁኔታ ለገበያ መቅረባቸውን በአዳማ ከተማ የሚገኙ ሸማቾችና ነጋዴዎች ገለጹ። በአዳማ ከተማ ለዘመን መለወጫ በዓል በተከፈተው ባዛር መሰረታዊ የፍጆታ እቃዎች በበቂ መጠን ለሸማቹ ህብረተሰብ ተደራሽ መሆናቸውን ያነጋገርናቸው አምራቾችና ሸማቾች ገልጸዋል።   የዲና ዱቄት ፋብሪካ የሽያጭ ተወካይ አቶ ጅማ ተንኮሉ እንደገለጹት፤ ፋብሪካቸው በከተማ አስተዳደሩ በተዘጋጀው ባዛር ላይ በመሳተፍ ለአዲስ ዓመት በዓል የሚሆኑ የምግብ እህሎችን በጥራትና በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እያቀረበ ይገኛል።   በፋብሪካው ለገበያ ከቀረቡት ምርቶች መካከል ቀይና ነጭ ጤፍ፣ የፍርኖ ዱቄት እንዲሁም የበቆሎ ዱቄት ተጠቃሾች ሲሆኑ፤ ምርቶቹ እንደ ሸማቹ ፍላጎትና አቅም በ5፣ በ10፣ በ25 እና በ50 ኪሎ ግራም መቅረባቸውን ገልጸዋል። የበዓል የፍጆታ ምርቶች በበቂ መጠንና በተመጣጣኝ ዋጋ መቅረቡ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል እንደ አቅሙ ሸምቶ በዓሉን በደስታ እንዲያከብር የጎላ አስተዋጽኦ እንዳለው አብራርተዋል። የጎልደን ፉል ዘይት ፋብሪካ የሽያጭ ሰራተኛ ቃልኪዳን ሽፈራው በበኩላቸው፤ ፋብሪካው መጪውን የ2019 አዲስ ዓመት አስመልክቶ የገበያ መረጋጋትን ለመፍጠር ሰፊ ዝግጅት ማድረጉን ገልጸዋል።   በዚህም መሰረት ከሁለት እስከ አምስት ሊትር መጠን ያለው የምግብ ዘይት በተመጣጣኝ ዋጋና በበቂ ሁኔታ በባዛሩ ማቅረቡን ተናግረዋል። ሸማቹ ህብረተሰብ በከተማዋ ወደተከፈቱ የበዓል ባዛሮች በመሄድ የሚፈልጋቸውን የፍጆታ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመት እንደሚችልም ገልጸዋል። ለበዓል ሲሸምቱ ካገኘናቸው ሸማቾች መካከል ወይዘሮ ዓለም ንጉሴ በበኩላቸው፤ ለበዓሉ የሚያስፈልጉ መሰረታዊ የፍጆታ እቃዎች በባዛሩ በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውን ገልጸዋል።   አምራች ኢንዱስትሪዎችና ነጋዴዎች በባዛሩ ላይ እያቀረቡት ያለው የፍጆታ ምርት የገበያ ዋጋን በማረጋጋት በኩል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ወይዘሮ ዓለም ገልጸዋል። ለበዓል ፍጆታ የሚሆን የምግብ ዘይት፣ ሽንኩርትና ሌሎችንም ማጣፈጫዎች በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመታቸውን ተናግረዋል። ሌላኛው ሸማች አቶ አክሊሉ ዘውዴ፤ የከተማ አስተዳደሩ ዘመን መለወጫ በዓልን ምክንያት በማድረግ ባዛር በማዘጋጀትና ከአቅራቢዎች ጋር በመቀናጀት ያለምንም ደላላ ጣልቃ ገብነት ምርቶች በቀጥታ ለሸማቹ እንዲደርሱ ማድረጉ የበዓል ገበያው እንዲረጋጋ ማድረጉን ገልጸዋል።   ይህም በዓሉን ምክንያት በማድረግ በሚፈጠር አላስፈላጊ የዋጋ ጭማሪ በህብረተሰቡ ላይ የሚደርሰውን ጫና እየቀነሰው መሆኑን አቶ አክሊሉ ተናግረዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ብዙነህ ግርማ እንደገለጹት፤ ኢንቨስትመንት ግሩፑ የዘመን መለወጫ በዓልን ምክንያት በማድረግ የተለያዩ የበዓል ፍጆታ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ ለማቅረብ የግብይት ባዛር አዘጋጅቷል።   በባዛሩ ላይ ከ300 የሚበልጡ አምራች ኢንዱስትሪዎች፣ መሰረታዊ ህብረት ስራ ማህበራት፣ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች እንዲሁም ነጋዴዎች መሳተፋቸውንም አቶ ብዙነህ አስታውቀዋል። አስተዳደሩም መጪውን የዘመን መለወጫ በዓል ምክንያት በማድረግ በገበያው ላይ የምርት አቅርቦት እጥረትና የዋጋ ንረት እንዳይከሰት እንዲሁም ህገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር ግብረ ሀይል አቋቁሞ እየሰራ መሆኑንም አብራርተዋል።
የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአንድነትና የጽናት ተሞክሮ ለቀጣይ ትላልቅ ፕሮጀክቶች መሠረት ይሆናል
Sep 8, 2026 350
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፡-የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን እውን ያደረገው የኢትዮጵያውያን የጋራ ጥረትና ጽናት ተሞክሮ በቀጣይ ለሚከናወኑ ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶች መሰረት እንደሚሆን የፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር) ገለጹ። ዋና ስራ አስፈጻሚው አረጋዊ በርሔ(ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ስኬት ከአንድ ተቋም ወይም ከአንድ ቡድን ጥረት የመነጨ ሳይሆን የኢትዮጵያውያን የጋራ ተሳትፎና ትብብር ውጤት ነው። ኢትዮጵያ በርካታ ድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ያሏት በመሆኑ የውሃ ሀብቷን በአግባቡ በመጠቀም ተጨማሪ የውሃና የኃይል ልማት ፕሮጀክቶችን ማልማት እንደምትችልም ገልጸዋል።   የውሃ ሀብትን ለኃይል ማመንጫነት በማዋል የሀገር ውስጥ የኃይል ፍላጎትን ከማሟላት ባሻገር ለቀጣናው ሀገራት ኤሌክትሪክ ሀይል በማቅረብ የውጭ ምንዛሬ ማስገኘት የሚያስችል እምቅ አቅም አለ ነው ያሉት። ይህን እምቅ አቅም ወደ ተጨባጭ ልማት ለመቀየር ዋነኛው መሠረት የሕዝብ ትብብርና ተሳትፎ መሆኑን ጠቁመው፤ በዚህም ትልቅ ሀገራዊ ዓላማዎችን ማሳካት እንደሚቻል የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ተሞክሮ ትልቅ ማሳያ መሆኑን አመልክተዋል። ዋናው ቁልፉ ነገር መተባበር እንደሆነ አመልክተው፣ በልማት ላይ ትኩረት ከተደረገ ኢትዮጵያን ትልቅ የልማትና የሥልጣኔ ደረጃ ላይ ማድረስ እንደሚቻልም ገልጸዋል።   የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታን እውን ለማድረግ የታየው የህዝብ ጽናት ታሪካዊ መሆኑን ጠቁመው፤ የተገኘው ተሞክሮ ኢትዮጵያ በራሷ አቅም ትላልቅ ፕሮጀክቶችን ማሳካት እንደምትችል ያረጋገጠ ነው ብለዋል። የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሂደት ኢትዮጵያውያን በአንድነት እና በጽናት ሲቆሙ ትልቅ ሀገራዊ ዓላማን ማሳካት እንደሚችሉ ያሳየ እንደሆነ አመልክተው፤ ይህ የትብብር እና የጽናት መንፈስ በቀጣይ በሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ላይም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስረድተዋል።
ግብፅ የምታስተጋባው ተከታታይ ጩኸት ኢትዮጵያ ወንዞቿን በማልማት ከመጠቀም የሚያግዳት አይደለም 
Sep 8, 2026 330
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፡-ግብፅ የምታስተጋባው ተከታታይ ጩኸት ኢትዮጵያ ወንዞቿን በማልማት የኤሌክትሪክ ኃይል በማመንጨትና በመስኖ ልማት ከመጠቀም እንደማያግዳት የቀድሞው የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር አምባሳደር አለማየሁ ተገኑ ገለጹ። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአፍሪካ ሕብረትን አጀንዳ 2063 ርዕይ የሚያሳካ፣ የራስ መተማመን መንፈስን ያጎናጸፈ የአፍሪካ ድል መሆኑንም ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት ግብፅ የምታስተጋባው ተከታታይ ጩኸት ኢትዮጵያ ወንዞቿን በማልማት የኤሌክትሪክ ኃይል ከማመንጨትና መስኖ ከመጠቀም የሚያግዳት እንዳልሆነም አስገንዝበዋል። አምባሳደር አለማየሁ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ታላቁን ሕዳሴ ግድብ ከመገንባቷ በፊት ለሺዎች ዘመናት የዓባይ ወንዝን ሳትጠቀም ቆይታለች።   ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝን አስመልክቶ የምታራምደውን የፍትሐዊና ምክንያታዊ ተጠቃሚነት መርህ በተለያዩ መድረኮች ከመግለጽም ባሻገር በጋራ የመጠቀም ጽኑ ፍላጎቷን ስታስረዳ መቆየቷን ገልጸዋል። የግብፅን ኢ-ምክንያታዊ የውሃ አጠቃቀም ክርክር ያስታወሱት አምባሳደር አለማየሁ፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ቆሞ እንመካከር እስከማለት የደረሰ እንደነበርም ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ታላቁን የሕዳሴ ግድብ ግንባታ እስከመጨረሻው ድረስ በማስቀጠል ምክንያታዊና ፍትሐዊ የውሃ ሀብት ተጠቃሚነት መርህ እንዲሰፍን ብርቱ ተጋድሎ ማድረጓን ጠቅሰዋል። ለዚህም በሀገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ግድቡን በራስ አቅም ለመገንባት ያደረጉት ከፍተኛ ድጋፍና ተጋድሎ በጀግንነት የታጀበና አስደናቂ መሆኑን አስታውሰዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአፍሪካ ሕብረትን አጀንዳ 2063 ርዕይ የሚያሳካ፣ የራስ መተማመን መንፈስን ያጎናጸፈ የአፍሪካ ድል መሆኑንም ገልጸዋል። የአፍሪካ ሀገራትም ሕዝብና የውስጥ አቅማቸውን በመጠቀም እንደ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መገንባት እንደሚችሉ ትምህርት የሰጠ የፓን አፍሪካኒዝም ፕሮጀክት መሆኑን አብራርተዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም. ሲመረቅ የጎረቤት ሀገራት የኢትዮጵያ ደስታ ተካፋይ የሆኑበትና የጋራ ተጠቃሚነትን ያበሰረ ወሳኝ ፕሮጀክት መሆኑን አንስተዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ከሀገር ውስጥ ባሻገር ለቀጣናው ሀገራት የፈጠረው የኃይል ትስስርም የዓባይ ወንዝን ኢ-ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ትርክት የሰበረ ድል መሆኑን አስረድተዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ፍጻሜም በግብፅና በታችኞቹ ተፋሰስ ሀገራት አስተማማኝ የውሃ ፍሰት በመፍጠር ምንም ዓይነት ጉዳት እንደማይደርስባቸው በተጨባጭ ያረጋገጠ መሆኑን አስረድተዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታም ድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን ፍትሐዊና ምክንያታዊ ተጠቃሚነት ትብብርና መርህ በማብሰር አዲስ ምዕራፍ የከፈተ ታሪካዊ ክስተት መሆኑን አብራርተዋል።   የታላቁ ሕዳሴ ግድብ የኢትዮጵያን በዓባይ ወንዝ ያለመጠቀም ኢ-ፍትሐዊ አካሄድን በማፍረስ የናይል ትብብር ማዕቀፍ ስምምነት ወደ ሥራ ማስገባት እንዳስቻለም አብራርተዋል። ግብፅ የኢትዮጵያን ዕድገትና ብልጽግና አትፈልግም ያሉት አምባሳደር አለማየሁ፤ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ተጠናቆም ግብፅ የምታስተጋባው ጩኸት የሀገሪቷን የፖለቲካ ሁኔታ ለማርገብ እንደሚጠቀሙበት አመልክተዋል። ለአብነትም በዓለም አቀፉ የፀጥታው ምክር ቤት ጭምር ታይቶ በማይታወቅ መልኩ በውሃ ጉዳይ ኢትዮጵያን መሞገቷን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያ በቀጣይ የምትገነባቸው ግድቦችም አስተማማኝ የውሃ ፍሰትን በመፍጠር የግብፅን የውሃ ብክነት እንደሚታደጉ አስረድተዋል። ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቶቿን ለመጠቀም የማንም ይሁንታ ሳያስፈልጋት ተጨማሪ ግድቦችን በመገንባት በመርህ ላይ በተመሠረተ መልኩ ልማቷን የማፋጠን ሙሉ መብት እንዳላት አስረድተዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር በየዓመቱ የምትተክላቸው ችግኞችም የስነ-ምኅዳር ደኅንነትን በመጠበቅ ለውሃ ሀብት ጥበቃ ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል ለዓባይ ተፋሰስ ጥበቃ ላበረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦም ግብፅ ካሳ መክፈል እንደሚኖርባት አስረድተዋል። ግብፅ ዓባይን ለሺዎች ዘመናት በብቸኝነት በመጠቀም ኢትዮጵያ ከልማት ወደኋላ እንድትቀር ላደረሰችባት በደልና ለአካባቢ ጥበቃ ለምታበረክተው አስተዋጽኦ ካሳ መክፈል እንዳለባትም ገልጸዋል።
በየዘርፉ ለተመዘገቡ ስኬታማ የልማት ተግባራት የጸጥታ አካላት ሚና ከፍተኛ ነው
Sep 8, 2026 273
ጅግጅጋ፤ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፡-በየዘርፉ ለተመዘገቡ ስኬታማ የልማት ተግባራት የጸጥታ አካላት ሚና ከፍተኛ መሆኑን የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ መሀመድ ገለጹ። ጳጉሜን 3 የጽናት ቀን በሶማሌ ክልል ደረጃ በጅግጅጋ ከተማ ተከብሯል።   በበአሉ ላይ የተገኙት የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ መሀመድ እንደገለጹት ፣የሀገርን ሰላም በማጽናት ልማትን ለማስቀጠል በሚደረግ ጥረት የጸጥታ አካላት ሚና ከፍተኛ ነው። እንደ ክልሉም ሆነ እንደ ሀገር ለተመዘገቡ ስኬታማ የልማት ተግባራት የጸጥታ አካላት ድርሻ የጎላ መሆኑን ጠቅሰዋል ። ጠንካራ ጽኑ መሠረት ያለው ሀገር ለመገንባት የህብረተሰቡ እና የጸጥታ አካላት የተቀናጀ ጥረት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው ቅንጅታዊ ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል ። በክልሉ የተጀመሩ የልማት ተግባራትን አጠናክሮ ለማስቀጠል ጽናት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ፍትህ ቢሮ ሀላፊ አቶ መሀመድናጂ መሐመድ ናቸው።   ጽናት ህዝቦች ችግሮችን የሚያልፉበትና ወደ አዲስ ዕድል የሚቀይሩበት ተግባር ነው ብለዋል። የሶማሌ ክልል ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ መሐመድ መሐሙድ በበኩላቸው፤ የጽናት ቀንን ስናከብር አባቶቻችን ያወረሱንን ሀገር በማጽናት ለትውልድ ለማስተላለፍ ቃላችንን በማደስ ሊሆን ይገባል ብለዋል። በበአሉ ላይ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች፣ የሰላምና ጸጥታ ዘርፍ አካላት፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ የኳታር ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች እንዲሳተፉ ጥሪ አቀረቡ
Sep 8, 2026 157
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፡- የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ የኳታር ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች እንዲሳተፉና የሁለቱ አገራት የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት እንዲጠናከር ጥሪ አቀረቡ። የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች ዱባይ እየተካሄደ ካለው ዓመታዊው ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ጉባኤ (AIM Congress) ጎን ለጎን የኳታር ቻምበር የቦርድ አባል አሊ ቢን አብዱላቲፍ አል ሚስናድ ጋር ዛሬ መወያየታቸውን የኢዜአ ሪፖርተር ከሥፍራው ዘግቧል።   ውይይቱ የኳታር ባለሀብቶች በኢትዮጵያ በተለይም በግብርና፣ በጤና፣ በመሠረተ ልማት ግንባታ፣ በማማከር አገልግሎትና በሌሎች የኢንቨስትመንት አማራጮች ተሳትፏቸውን ማሳደግ በሚችሉባቸው ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርጓል። ፕሬዚዳንት ታዬ በወቅቱ፣ ኢትዮጵያ የውጭ ባለሀብቶችን ለመሳብና ምቹ የኢንቨስትመንት ከባቢ ለመፍጠር መንግሥት ትኩረት አድርጎ የሚሠራቸውን ሥራዎች አብራርተዋል። በዚህም የኳታር ባለሀብቶች በአገሪቱ ያሉትን ምቹና አስቻይ የኢንቨስትመንት አማራጮች እንዲጠቀሙና ግንኙነታቸው ይበልጥ እንዲጠናከር ጥሪ አድርገዋል።   የኳታር ቻምበር የቦርድ አባል አሊ ቢን አብዱላቲፍ አል ሚስናድም በበኩላቸው እንደገለጹት፤ የኳታር ባለሀብቶች በግብርና፣ በጤና፣ በመሠረተ ልማት ግንባታ በተለይም በቤቶች ግንባታና በዲጂታል ልማት ዘርፍ ለመሳተፍ ፍላጎት አላቸው። በኢትዮጵያ ያለውን ምቹ የኢንቨስትመንት ከባቢ የኳታር ባለሀብቶች እንዲጠቀሙበት ለማድረግና በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሠሩም ተናግረዋል።
ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት የማጠናቀቅ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል
Sep 8, 2026 223
ወልቂጤ፤ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ በጥራትና በፍጥነት የማጠናቀቅ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ የጉራጌ ዞን አስተዳደር በወልቂጤ ከተማ በ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ ያስገነባውን ባለ ዘጠኝ ወለል የአስተዳደር ሕንጻ ዛሬ መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።   በዚህ ወቅት ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) እንደገለፁት፣ በአሁኑ ወቅት በክልሉ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ በጥራትና በፍጥነት ተጠናቀው ለአገልግሎት እየበቁ ይገኛሉ። ይህም የህዝብ ተጠቃሚነትን ከማረጋገጥ አንጻር ጉልህ ሚና እየተጫወተ በመሆኑ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ በጥራትና በፍጥነት የማጠናቀቅ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በክልሉ በዕቅድ የሚመራና በፅናት የሚሰራ አመራርና ሠራተኛ በየደረጃው በመኖሩ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ፣ በጥራት እና በፍጥነት እንዲጠናቀቁ ማድረጉንም ተናግረዋል።   ዛሬ ግንባታው ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቃው የጉራጌ ዞን አስተዳደር ሕንጻ ለእዚህ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው፣ ሕንጻው አስተዳደሩ ለህብረተሰቡ የሚሰጠውን አገልግሎት በማዘመንና በማቀላጠፍ በኩል ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል፡፡ በክልሉ የልማት ሥራዎች ላይ የህብረተሰቡ ተሳትፎ በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉን የጠቆሙት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ ጉራጌ ዞን በግብርና፣ በትምህርት፣ በጤና እንዲሁም በፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ግንባር ቀደም ተሳትፎ እያደረገ ይገኛል ብለዋል።   የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ በበኩላቸው፤ በመደመር መንግስት እይታ ፈተናዎችን በመቋቋም የነገን ትውልድ ጭምር ታሳቢ ያደረጉ ፕሮጀክቶች እውን እየተደረጉ ይገኛሉ ብለዋል። ለዚህም በ2 ሺህ ካሬ ሜትር መሬት ላይ ያረፈውና ለምረቃ የበቃው ባለዘጠኝ ወለል የጉራጌ ዞን አስተዳደር ሕንጻ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፣ ሕንጻው ዘመኑን ታሳቢ ያደረገ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ብለዋል። በዞኑ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎችን በማስፋፋት ለህብረተሰቡ ጊዜና ወጪን የሚቆጥብ ፈጣን አገልግሎት ለመስጠት የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል ብለዋል። በዞኑ የአስተዳደር ሕንጻ ምረቃ ሥነስርዓት ላይ ከፌደራል፣ ከክልል እና ከአጎራባች ዞንና ልዩ ወረዳዎች የመጡ የሥራ ሃላፊዎችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
የሕዳሴ ግድብ ስኬት የኢትዮጵያውያን የጽናት ውጤት ነው
Sep 8, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፦ በሕዳሴ ግድብ የተገኘው ስኬት በመላ ኢትዮጵያውያን የጋራ ጥረት፣ ጽናትና ተሳትፎ የተገኘ መሆኑን የውኃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ (ዶ/ር) ገለጹ። ሕዳሴ ግድብ ግንባታን በውጤታማነት ለማጠናቀቅ የሕዝብ ተሳትፎን በማስተባበር በኩል ልዩ ልዩ ተግባራትን ሲያከናወኑ የቆዩ አካላትን የማመስገንና የእውቅና መርሃ ግብር ተካሄዷል።   ሚኒስትር ዴኤታው አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያውያን በአንድነት በመቆም የአባይን ውኃ ለልማትና ለሀገራዊ ጥቅም ለማዋል ያደረጉት ጥረት ትልቅ ውጤት አስገኝቷል። የግድብ ግንባታ የኢትዮጵያውያን የጋራ ጽናትና ተሳትፎ ማሳያ ነው ሲሉም ገልጸዋል። በግድቡ ግንባታ ሂደት መላው ኢትዮጵያውያን በሀገር ውስጥና በውጭ የሚኖረው ዳያስፖራ በገንዘብ፣ በእውቀትና በሞራል እንዲሁም በተለያየ መልኩ ድጋፍ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የትውልድ አደራ፣ የሉዓላዊነታችን ማረጋገጫና የኢትዮጵያውያን የጋራ ጽናት ማሳያ ፕሮጀክት ነው ሲሉም ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል።   የሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የኢትዮጵያ ሕዝብና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በሞራል፣ በገንዘብ፣ በጉልበት፣ በአካባቢ ጥበቃና በሕዝብ ዲፕሎማሲ ያደረጉት ተሳትፎ ግድቡ እውን እንዲሆን ወሳኝ ሚና እንደነበረው ተናግረዋል። የግድቡ ግንባታ የኢትዮጵያውያን የጋራ ርብርብ ማዕከል ሆኖ መቆየቱን ጠቁመው፣ ሕዝቡ በጋራ በመቆም ለስኬት ማብቃቱንም አስታውሰዋል። የሕዝብ ተሳትፎ ከገንዘብ ማሰባሰብ ባሻገር የኢትዮጵያን እውነታ ለዓለም ማስረዳት ላይ የጎላ ሚና እንደነበረውም ጠቅሰዋል። በሌላ በኩል በግድቡ ግንባታና በሕዝብ ተሳትፎ ሂደት የተከናወኑ ተግባራት፣ ያጋጠሙ ፈተናዎችና የተገኙ የድል ታሪኮችን የሚዘክር "ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የፅናት ተምሳሌት" የተሰኘ ባለ199 ገጽ መጽሐፍ በመርሃ ግብሩ ተመርቋል። መጽሐፉ የሕዳሴ ግድብን ለማሳካት የተደረገውን ትግል፣ የሕዝቡን ተሳትፎና የጋራ ጥረት በማስመዝገብ ለቀጣዩ ትውልድ ታሪካዊ ማስታወሻ ሆኖ እንዲያገለግል መዘጋጀቱም ተገልጿል።
የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ከ2 ሺህ 500 በላይ የሚሆኑ ሱቆችን ግንባታ በይፋ አስጀመረ
Sep 8, 2026 62
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፦ የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በዛሬው ዕለት ከ2 ሺህ 500 በላይ የሚሆኑ ሱቆችን ግንባታ በይፋ አስጀምሯል። የኮርፖሬሽኑ ዋና ስራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ተቋሙ በተለያዩ መልኮች ከነበረበት አስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ በሪፎርም ወደ ትርፋማ ምዕራፍ መሸጋገሩን ገልጸዋል። በዚህም ተቋሙ ትርፉን በ42 እጥፍ ማሳደግ መቻሉንና በዛሬው ዕለትም ከ2ሺ 500 በላይ የሚሆኑ ሱቆችን ግንባታ በይፋ ማስጀመሩን ተናግረዋል።   በዛሬው ዕለት የተጀመረው ግንባታ በ4 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ወጪ በአልሚዎች ትብብር የሚገነባ ሲሆን ባለስድስት ወለል ሕንፃና በቂ የመኪና ማቆሚያ፣ ዘመናዊ መዝናኛ ቦታዎችን ከሱቆች ጋር የያዘ ነው። ዋና ስራ አስፈጻሚው በሱቆቹ ለልማቱ የሚነሱት 230 ነባር ተከራዮችን ጨምሮ ተጨማሪ ዜጎች እድል እንደሚፈጠርላቸውም አስታውቀዋል። ኮርፖሬሽኑ በአንድ ዓመት ውስጥ አስር ህንፃዎችን ለማጠናቀቅ እቅድ መያዙንና ወደ 10 ሺ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ እድል መፍጠር የሚችሉ ግንባታዎች እየተሰሩ እንደሚገኙም አንስተዋል። በሌላ በኩል የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በመርካቶ ያስገነባቸውን 399 ሱቆችንም በዛሬው ዕለት አስመርቋል።
ለዘመን መለወጫ በዓል ከተዘጋጀው ባዛር አስፈላጊ ምርቶችን በአንድ ቦታ እና በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኘን ነው - ሸማቾች
Sep 8, 2026 98
ጭሮ፣ ጳጉሜን 3/2018 (ኢዜአ)፡-በጭሮ ከተማ ለዘመን መለወጫ በዓል በተዘጋጀው ባዛር ለአዲሱ ዓመት የሚያስፈልጓቸውን ምርቶች በአንድ ቦታና በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኙ መሆናቸውን ሸማቾች ገለጹ። በዓላትን ምክንያት በማድረግ የሚዘጋጁ የንግድ ባዛሮችና ኤግዚቢሽኖች በኅብረተሰቡ ላይ የሚፈጠረውን የኢኮኖሚ ጫና ለመቀነስ እና የገበያ መረጋጋትን ለመፍጠር ትልቅ ሚና አላቸው። በተለይም ከአምራቾች፣ ከኢንዱስትሪዎችና ከአቅራቢዎች ምርቶችን በቀጥታ ለሸማቹ ማቅረብ መቻሉ አላስፈላጊ ደላሎችን በማስቀረት የዋጋ ንረትን ለመግታት ያስችላል።   በጭሮ ከተማ የተዘጋጀው የበዓል ባዛርም ኅብረተሰቡ ለአዲሱ ዓመት የሚያስፈልጉትን የግብርና እና የኢንዱስትሪ ፍጆታዎችን በአንድ ማዕከል እና ከወትሮው ገበያ በተሻለ በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ የታለመ ነው። ይህም የሸማቹን የመግዛት አቅም ከማሳደጉም በላይ፣ የበዓሉ ገበያ ሰላማዊና የተረጋጋ እንዲሆን የሚያደርግ የልማትና የንግድ ትስስር እንቅስቃሴ አካል ነው። በባዛሩ ከተገኙት ሸማቾች መካከል አንዳንዶቹ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ በተለይም በበዓላት ወቅት በበዓል ገበያ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ የሚታይባቸው ምርቶች ባዛሩ ላይ በተመጣጣኝና አነስተኛ ዋጋ እንደቀረቡላቸው ገልጸዋል። ከሸማቾቹ መካከል አቶ ሽመልስ ብሩ፤ በመደበኛው ገበያ እስከ 900 ብር የሚሸጥ መካከለኛ ዶሮ በባዛሩ በ600 ብር መግዛታቸውን ገልጸው፣ እንዲህ ያሉ ባዛሮች በበዓላት ወቅት መዘጋጀታቸው ለሸማቹ ትልቅ እፎይታ እንደሚሰጥ ጠቁመዋል። እንደ ሽንኩርት፣ ዶሮ እና እንቁላል ያሉ የበዓል ምርቶች በብዛትና በተመጣጣኝ ዋጋ መቅረባቸው በዓሉን በተሟላ እና በድምቀት ለማክበር የሚያግዛቸው መሆኑን ተናግረዋል። የበዓል ወቅቱን አስመልከተው አስተያየታቸውን የሰጡት አቶ መስፍን ሀይሌ፣ በአነስተኛ ዋጋ የቀረበው ምርት በዓሉን በድምቀት ለማክበር እንደሚያስችላቸው ገልጸዋል።   ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ ደጀኔ ጋሪ በበኩላቸው፣ በመደበኛው ገበያ እስከ 1 ሺህ 100 ብር ይሸጥ የነበረውን የሦስት ሊትር ዘይት በ950 ብር መግዛታቸውን ተናግረዋል። ይህም ለበዓሉ የሚያስፈልጉ ሌሎች ምርቶችን ለመግዛት ተጨማሪ አቅም እንደሆናቸው ገልጸዋል። ሸማቾቹ እንደሚሉት፣ በተለይም ዘይት በመደበኛው ገበያ ከሚገኘው ዋጋ በ170 ብር ቅናሽ የቀረበ ሲሆን፣ እንቁላልም በአንዱ የአምስት ብር ቅናሽ ተደርጎበታል። የጭሮ ከተማ ንግድ፣ ሥራ ፈጠራና ኢንቨስትመንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ተወካይ አቶ አደም ዩሱፍ፣ ህብረተሰቡ የሕብረት ሥራ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ ከትናንት ጀምሮ እስከ ጳጉሜ 5 የሚቆይ ባዛር መዘጋጀቱን ገልጸዋል።   በባዛሩ ከጭሮ ከተማና ከጭሮ ወረዳ የተወጣጡ 14 አምራቾችና አከፋፋዮች እንዲሁም አንድ የሕብረት ሥራ ዩኒየን ምርቶቻቸውን ለሸማቾች እያቀረቡ እንደሚገኙም ጠቁመዋል። በባዛሩ ጤፍ፣ ሩዝ፣ ስንዴ፣ ሽንኩርት፣ ዘይት፣ እንቁላልና ዶሮን ጨምሮ ሌሎች ለዘመን መለወጫ በዓል የሚያስፈልጉ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋና በበቂ መጠን መቅረባቸውንም አቶ አደም ገልጸዋል።  
ለዘመን መለወጫ የእርድ እንስሳት እና የበዓል ፍጆታ ቁሶች በበቂ ሁኔታ ቀርበዋል
Sep 8, 2026 122
ጉደር፤ ጳጉሜን 3/2018(ኢዜአ)፡- ለዘመን መለወጫ የበዓል ገበያ የእርድ እንስሳት እና የተለያዩ የበዓል ፍጆታ ምርቶች አቅርቦት በቂ መሆኑን በምዕራብ ሸዋ ዞን ጉደር ከተማ ነጋዴዎችና ሸማቾች አስታወቁ። የዘመን መለወጫ በዓል ሲቃረብ በየአካባቢው የሚከፈቱ የበዓል ገበያዎች ከፍተኛ የህዝብ እንቅስቃሴና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የሚታይባቸው ናቸው።   በተለይም የገበያውን ፍላጎትና አቅርቦት ለማጣጣም ከተለያዩ ክልሎች ወደ ዋና ዋና ከተሞች የሚገቡ የእርድ እንስሳት እንዲሁም የመሠረታዊ ምግብ ነክ ቁሶች ስርጭት የተሻለ እንዲሆን በሁሉም አካላት ጥረት ተደርጓል። የአቅርቦቱ ማደግ ደግሞ አላስፈላጊ የዋጋ ጭማሪን በመግታት ህብረተሰቡ እንደየምርጫውና እንደአቅሙ ገበያ ወጥቶ እንዲሸምት መንገድ አመቻችቷል።   ኢዜአ ያነጋገራቸው የጉደር ከተማ ነጋዴዎችና ሸማቾች፤ ለአዲሱ ዓመት በዓል የሚሆኑ የእርድ እንስሳት እና የተለያዩ የፍጆታ ምርቶች በበቂ ሁኔታ ለገበያ በመቅረባቸው፣ ህብረተሰቡ እንደየአቅሙ እየተገበያየ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በከተማው የቁም እንስሳት ገበያ ከተገኙት ሸማቾች መካከል አቶ ንጉሴ ከፈኒ፤ ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የተሻለ አቅርቦትና የተረጋጋ ግብይት መኖሩን ገልጸዋል። የዘንድሮው የአዲሱ ዓመት የበዓል ገበያ ዋጋ ተመጣጣኝ በመሆኑ ህብረተሰቡ እንደየአቅሙ እየተገበያየ እንደሚገኝ በመጥቀስ፤ የምርቶች አቅርቦትም በስፋት እንደሚገኝ ተናግረዋል። ሌላው አስተያየት ሰጪ ነጋዴ አቶ አሰፋ ሽብሩ በበኩላቸው፤ የእርድ እንስሳት አቅርቦቱ በቂ ቢሆንም መጠነኛ የዋጋ ጭማሪ መኖሩን ጠቁመው፣ በገበያው ከፍተኛው የሰባ በሬ እስከ 150 ሺህ ብር እየተሸጠ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዓሉ የደስታና የመረዳዳት እንዲሆንም ያላቸው ከሌላቸው ጋር በመቋደስ ማሳለፍ እንደሚገባ ገልጸዋል። የበዓሉ ገበያ የተረጋጋ መሆኑንና የአትክልትና ፍራፍሬ አቅርቦት በብዛትና በጥራት መኖሩን የገለፁት ወይዘሮ አስካለች አለሙ ናቸው፡፡   በተጨማሪም አላስፈላጊ የዋጋ ንረት እንዳይኖር የሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ቁጥጥር እያደረጉ መሆኑን ጠቁመው፣ እስካሁን ጥሩ የግብይት እንቅስቃሴ መኖሩን ገልጸዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን ንግድ ጽሕፈት ቤት ተወካይ አቶ ተሰማ ኩምሳ፤ ለበዓሉ ከዞን እስከ ቀበሌ የሚደርስ ኮሚቴ በማደራጀት ህብረተሰቡ የበዓል ፍጆታ ምርቶችንና የእርድ እንስሳትን ያለ አቅርቦት እጥረት እንዲያገኝ መደረጉን ገልጸዋል። በግብይት ሂደቱ ህገ-ወጥ እንቅስቃሴዎች ከተስተዋሉ ህብረተሰቡ ጥቆማ መስጠት እንደሚችል ያነሱት ተወካዩ፣ በሁሉም አካባቢዎች ጥብቅ የቁጥጥርና ክትትል ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን አረጋግጠዋል። አምራችና ሸማች በቀጥታ የሚገናኙባቸው የገበያ ማዕከላት በመቋቋማቸው ህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲገበያይ እድል መፈጠሩን ያነሱት ተወካዩ፣ ለአዲሱ ዓመት በዓሉ የዶሮ፣ የበግና የፍየል አቅርቦት በስፋት መኖሩን ጠቁመዋል።    
በክልሉ በቱሪዝም ዘርፍ 978 ሚሊዮን ብር ገቢ ተገኝቷል
Sep 7, 2026 652
ጂንካ፥ ጳጉሜ 2/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት አመት በቱሪዝም ዘርፍ 978 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን የክልሉ ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ወይኒቱ መልኩ በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት አመት ከቱሪዝም ዘርፍ 500 ሚሊዮን ብር ገቢ ለማግኘት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን አስታውሰዋል። ይሁን እንጂ ለዘርፉ በተሰጠው ትኩረት ከእቅድ በላይ 978 ሚሊዮን ብር መገኘቱን ተናግረዋል። በክልሉ የቱሪዝም መዳረሻዎችን የማልማትና የማስተዋወቅ ስራ በስፋት በመሰራቱና የጎብኚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ለገቢው ማደግ በምክንያትነት ጠቅሰዋል።   የሙሩሌ የቁጥጥር አደን ቦታ፣ የማጎና የማዜ ብሔራዊ ፓርኮች የኮንሶ ባህላዊ መልክዓ ምድር ዓለም አቀፍ መካነ ቅርስ በክልሉ ከሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎች ዋነኞቹ እንደሆኑ ጠቁመዋል። የአርባምንጭ አዞ እርባታ፣ የባንባላ ተንጠልጣይ ድልድይ፣ የዳሞ ተራራና የጌዴኦ ትክል ድንጋዮች መካነ ቅርስም በስፋት እየተጎበኙ ያሉ የመስህብ ስፍራዎች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በበጀት አመቱ 13 ሚሊዮን የሀገር ውስጥና የውጪ ቱሪስቶች የመስህብ ስፍራዎቹን መጎብኘታቸውን ተናግረዋል።   በክልሉ የጎብኚዎች ቁጥር መጨመርም ለቢዝነስ ቱሪዝም መነቃቃት እና ለስራ እድል ፈጠራ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስታውቀዋል። የማጎ ብሔራዊ ፓርክ አስተዳዳሪ አቶ ኤርቦር ሌለ በበኩላቸው ፓርኩን ለመመልከት ወደ ስፍራው የሚመጡ ጎብኚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ተናግረዋል። ፓርኩ ከ80 በላይ አጥቢ፣ ከ250 በላይ የአዕዋፍና 14 ዓይነት የዓሣ ዝርያዎችን የያዘ መሆኑን አመልክተዋል።  
በአዲስ አበባ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የሀገሪቱን የማንሰራራት ጉዞ የሚያፋጥኑ ናቸው
Sep 7, 2026 621
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ) ፦ በአዲስ አበባ የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎችና ሌሎች የመሠረተ ልማት ሥራዎች የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ የሚያፋጥኑ መሆናቸውን ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጳጉሜን 02 "የማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በአዲስ አበባ የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎችንና የመሠረተ ልማት ሥራዎችን ለተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች አስጎብኝቷል።   በጉብኝት መርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉ ጎብኚዎች በአዲስ አበባ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ከተማዋ ለአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ እንድትሆን ያስቻሉ ናቸው ብለዋል፡፡ አስተያየት ሰጪ ሻምበል ዋኘው አባይ እንዳሉትም ከተማዋ ከዚህ ቀደም ከነበራት ገጽታ በተለየ መልኩ ውብና ጽዱ መሆኗን ገልጸው፤ የወንዝ ዳርቻ፣ የኮሪደር ልማትና የቱሪዝም መዳረሻዎች የሀገሪቱን ዕድገት የሚያንሰራሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። አቶ ገዛኸኝ አሰፋ በበኩላቸው የመሠረተ ልማት ሥራዎቹ ለዜጎች የሥራ ዕድል የፈጠሩ፣ ለነዋሪዎችና ለጎብኚዎች ምቹ አካባቢን የፈጠሩ መሆናቸውን በአካል ማረጋገጣቸውን ገልጸዋል፡፡ እነኚህም የኢትዮጵያን የማንሰራራት ግስጋሴ የሚያፋጥኑ ናቸው ብለዋል፡፡ የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን በመገናኛ ብዙኃን ከማየት ባለፈ በአካል መጥተው በመጎብኘታቸው መደሰታቸውን የገለጹት ሐጂ ሸምሱ አባስ ፤ የከተማዋ ዕድገት ለሀገር ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሙኒኬሽን ኃላፊ ልደት ሙለታ ጳጉሜን 02 "የማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በለውጡ ዓመታት ለነዋሪዎች ውብና ጽዱ ከተማን ለመፍጠርና በቱሪዝም ዘርፍ የተከናወኑ ሥራዎችን ማስጎብኘታቸውን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎች፣ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ተግባራት የሀገሪቱን ዕድገት ያረጋገጡ መሆናቸውንም ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጳጉሜን 02 "የማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በአዲስ አበባ የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎችንና የመሠረተ ልማት ሥራዎችን ለተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች አስጎብኝቷል። በጉብኝት መርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉ ጎብኚዎች በአዲስ አበባ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ከተማዋ ለአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ እንድትሆን ያስቻሉ ናቸው ብለዋል፡፡   አስተያየት ሰጪ ሻምበል ዋኘው አባይ እንዳሉትም ከተማዋ ከዚህ ቀደም ከነበራት ገጽታ በተለየ መልኩ ውብና ጽዱ መሆኗን ገልጸው፤ የወንዝ ዳርቻ፣ የኮሪደር ልማትና የቱሪዝም መዳረሻዎች የሀገሪቱን ዕድገት የሚያንሰራሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። አቶ ገዛኸኝ አሰፋ በበኩላቸው የመሠረተ ልማት ሥራዎቹ ለዜጎች የሥራ ዕድል የፈጠሩ፣ ለነዋሪዎችና ለጎብኚዎች ምቹ አካባቢን የፈጠሩ መሆናቸውን በአካል ማረጋገጣቸውን ገልጸዋል፡፡ እነኚህም የኢትዮጵያን የማንሰራራት ግስጋሴ የሚያፋጥኑ ናቸው ብለዋል፡፡ የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን በመገናኛ ብዙኃን ከማየት ባለፈ በአካል መጥተው በመጎብኘታቸው መደሰታቸውን የገለጹት ሐጂ ሸምሱ አባስ ፤ የከተማዋ ዕድገት ለሀገር ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሙኒኬሽን ኃላፊ ልደት ሙለታ ጳጉሜን 02 "የማንሰራራት ቀን"ን ምክንያት በማድረግ በለውጡ ዓመታት ለነዋሪዎች ውብና ጽዱ ከተማን ለመፍጠርና በቱሪዝም ዘርፍ የተከናወኑ ሥራዎችን ማስጎብኘታቸውን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎች፣ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ተግባራት የሀገሪቱን ዕድገት ያረጋገጡ መሆናቸውንም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም