ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በሀረሪ ክልል ክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራን ለማጎልበት በትኩረት ይሰራል
Aug 4, 2026 127
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 28/2018(ኢዜአ) ፦ በሀረሪ ክልል ክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራን በማጎልበትና የስራ ፈላጊዎችን የስራ ባህል ማሳደግ ላይ በትኩረት እንደሚሰራ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የክልሉ የስራ እድል ፈጠራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ወይዘሮ ሮዛ ኡመር ገለጹ። የክልሉ የስራ እድል ፈጠራ ምክር ቤት የ2018 በጀት አመት የስራ እድል ፈጠራ አፈጻጸም ሪፖርት እና የ2019 በጀት አመት እቅድ ላይ ውይይት አካሂዷል።   ሰብሳቢዋ በመድረኩ ላይ በክልሉ የስራ አጥነት ችግርን ለመፍታትና አዳዲስ ቋሚ የስራ እድሎች ለመፍጠር ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራን በማጎልበት እንዲሁም የስራ ፈላጊዎችን የስራ ባህልና ግንዛቤ ማስፋት ከቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ መካከል መሆኑንም ወይዘሮ ሮዛ ተናግረዋል። በተለይም ገበያ ላይ ተፈላጊ የሆኑ የክህሎት ስልጠናዎችን ከመስጠት ጀምሮ የዜጎችን የስራ ባህል በማሳደግ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ተጠቃሚነታቸውን በዘላቂነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራም ጠቁመዋል። በ2019 የበጀት አመት እቅድን ለማሳካት በሚከወኑ ስራዎች የሚገጥሙ ውስንነቶችን ለመቅረፍ በትኩረት መንቀሳቀስ እንደሚገባ ገልጸው የሚመለከታቸው አካላትም በቅንጅት መስራት እንደሚኖርባቸው አሳስበዋል። በዚህም በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች ለስራ እድል ፈጠራ ዘርፍ ከእቅድ ጀምሮ እስከ አፈጻጸሙ ድረስ ቅድሚያ በመስጠት በልዩ ትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ ወይዘሮ ሮዛ ተናግረዋል፡፡   የክልሉ የኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኢስማኢል ዩሱፍ ባቀረቡት ሪፖርት እንዳመላከቱት በስራ እድል ፈጠራና ስልጠና ዙሪያ ከልማት አጋር አካላት፣ ከመንግስትና ከግል ሴክተሮች ጋር በቅንጅት ሲሰራ ቆይቷል። በተጠናቀቀው የበጀት አመትም 11 ሺህ ቋሚ የስራ እድሎችን በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በአገልግሎትና በውጭ ሀገር ስራ ስምሪት በገጠርና በከተማ ለሚገኙ ዜጎች መመቻቸቱ ተገልጿል። በተፈጠረው የስራ እድልም በዋናነት ወጣቶች፣ ሴቶች፣ አካል ጉዳተኞች እና ከስደት ተመላሽ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የማኅበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ነው
Aug 4, 2026 133
ቡታጅራ ፤ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ገለፀ። በቢሮው "አንድነት ለፅዳት፣ ትጋት ለአገልግሎት፣ ውሳኔ ለልማት" በሚል መሪ ሐሳብ የተዘጋጀ የሴክተሩ የምክክር መድረክ በቡታጅራ ከተማ ተካሄዷል።   በወቅቱም የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ስንታየሁ ወልደሚካኤል እንዳሉት በክልሉ የማኅበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ነው። በዚህም ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸው በኮሪደር ልማትና የሚሰጡ አገልግሎቶችን በማዘመን ረገድ የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። የስልጤ ዞን ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን መምሪያ ኃላፊ አቶ አብዱልሰመድ አብደላ በበኩላቸው በዞኑ ዘመናዊና የተሳለጠ አገልግሎቶችን በመስጠት የተገልጋይ እርካታን ለማረጋገጥ የሚያስችል ስራ እየተሠራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   የኮሪደር ልማት ሥራ ከተሞችን ምቹ፣ ፅዱና ተመራጭ ከማድረግ ባለፈ የገጠር ቀበሌዎች ለኑሮ የተመቹና የወደፊቱን የከተሞች ዕድገት ታሳቢ ባደረገ መልኩ እንዲለሙ እየተደረገ ነው ብለዋል። ለዚህም ስኬት በዞኑ በሚገኙ 3 ወረዳዎች የአርሶ አደሩን የአኗኗር ዘዬ የሚቀይሩ 24 ቤቶች መገንባታቸውንና በዕቅድ የተያዙትን ቀሪ ቤቶች ለማጠናቀቅ እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በከተማው በመሬት ዘርፍ በሚሰጡ አገልግሎቶች የሚነሱ የማኅበረሰቡን ቅሬታዎች ለመፍታት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው ያሉት ደግሞ የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሽጉጤ ናቸው።   በተለይም 45 የሚጠጉ የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች በመሶብ የአንድ ማዕከል እንዲሰጡ መደረጉ ለውጥ እንዳመጣም ጠቁመዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮችና የዘርፉ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።  
በክልሉ የከተሞችን እድገትና የገጠር የልማት ሽግግር ዘላቂነት ታሳቢ ያደረገ ፕላን በማዘጋጀት እየተተገበረ ነው
Aug 4, 2026 144
ባህር ዳር፤ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የወቅቱን የከተሞችን እድገትና የገጠር የልማት ሽግግር ዘላቂነት ታሳቢ ያደረገ ፕላን በማዘጋጀት እየተተገበረ እንደሚገኝ የክልሉ ፕላን ኢንስቲትዩት ገለጸ። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ምትኩ ዓለማየሁ (ዶ/ር) ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳሉት፤ በክልሉ ከተሞችና የገጠር ቀበሌዎች መጪውን እድገትና የሕዝብ አኗኗር መሠረት ተደርጎ እየተሠራ ነው። ከተሞች ካላቸው ፈጣን እድገት ጋር ተያይዞ ዘላቂነት ያለው የመሠረተ ልማት ግንባታ፣ የመኖሪያ አካባቢዎች፣ ማህበራዊ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማትንና ሌሎችንም ሁኔታዎች ባሟላ መንገድ መጪውን ጊዜ ታሳቢ በማድረግ በፕላን እንዲመሩ እየተደረገ ይገኛል። እንዲሁም የገጠር ሽግግርን የተሳካ ለማድረግ የገጠር ቀበሌ ማዕከላት በፕላን ላይ መሠረት አድርገው እንዲቋቋሙ በቅንጅት እየተሠራ እንደሆነም አንስተዋል። በተለይም የኮሪደር ልማት ኢኒሼቲቭ፣ ከተሞችና የገጠር አካባቢዎች በዘላቂ ፕላን እንዲመሩ አስገዳጅ ከመሆኑም በላይ ለዘላቂ እድገት መልካም ሆኖ መገኘቱን ተናግረዋል። ኢንስቲትዩቱ በ2018 በጀት ዓመት ተቋማዊ ሪፎርም ከማድረግ ባሻገር ለአሠራር የሚያግዙ የሕግ ማሻሻያዎችን የማድረግ ሥራ ተሠርቷል ብለዋል። እንዲሁም 137 የተለያየ ዓይነት ፕላን በማዘጋጀት ወደ ትግበራ እንዲገባ መደረጉን ጠቅሰው፤ ከእነዚሁ ውስጥ 37 የሚሆኑት የገጠር ቀበሌ ማዕከላት ፕላኖች መሆናቸውን ገልጸዋል። በፕላን ዝግጅቱ ከ14 ሺህ በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ማሳተፍ መቻሉን ጠቅሰው፤ የፕላን ትግበራ፣ ክትትልና ቁጥጥር ሥራ መካሄዱንም አብራርተዋል። ኢንስቲትዩቱ በ2019 በጀት ዓመትም 187 የተለያየ ዓይነት ፕላን ለማዘጋጀት አቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን ጠቅሰዋል። የፕላን ዝግጅቱ የክልሉን የ25 ዓመት አሻጋሪ የልማትና የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ መሠረት በማድረግ እየተተገበረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ከሚዘጋጀው ፕላን ውስጥም 130 ያህሉ የገጠር ቀበሌ ማዕከላት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ይህም መንግሥት ለገጠር ሽግግር የሰጠውን ትኩረት መሠረት በማድረግ የሚሠራ ነው ብለዋል። የገጠር ማዕከላቱ የመኖሪያ አካባቢዎችን፣ መሠረተ ልማትን፣ የገበያ ቦታዎችን፣ ማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማትንና የአርሶ አደሩን የግብርና ሥራ በሚያሳልጥ አግባብ የሚሠሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። ተዘጋጅተው የሚቀርቡ ፕላኖች ወደ ትግበራ ሲገቡ በየደረጃው የሚገኝ አመራርና ባለሙያ ሕብረተሰቡን በማሳተፍ መተግበር እንዳለበትም ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል።      
ታዋቂው ሲ ኤን ኤን ቴሌቪዥን ጣቢያ ስለ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ
Aug 4, 2026 309
ታዋቂው የሲኤንኤን የቴሌቪዥን ጣቢያ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ከኢትዮጵያ ባለፈ የቀጣናው ሀገራትን የኢነርጂ ተጠቃሚ ያደረገ ግዙፍ ፕሮጀክት መሆኑን በዘገባው አስቃኝቷል። ግድቡ በሚሊየኖች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ብርሃን ያደረሰ መሆኑንም አመላክቷል። በሲኤንኤን ዘጋቢ የሆነችው ቪክቶሪያ ሩባዲሪ ባሰናዳችው ዘገባ÷ ወደ ጉባ በማቅናት የግድቡን እውነታ አስቃኝታለች። በዚህም በሺዎች የሚቆጠሩ በርካታ የምህንድስና ባለሙያዎች እና የግንባታ ባለሙያዎች ሸለቋማ የሆነውን አካባቢ ወደ አፍሪካ ግዙፍ ግድብ መቀየራቸውን ገልጻለች። ግድቡ የምህንድስና ልህቀት የታየበት ነውም ብላለች። ከ14 ዓመታት የግንባታ ቆይታ በኋላ ህዳሴ ግድብ እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር መስከረም 2025 መመረቁን ገልጻለች። ግድቡ በኢትዮጵያውያን ድጋፍ፣ የመንግስት ፋይናንስ፣ ቦንዶች እና የተለያዩ የሀገር ውስጥ የፋይናንስ አማራጮች በኢትዮጵያዊያን አቅም መገንባቱን ተናግራለች። ይህ ግዙፍ ግድብ ለሚሊዮኖች ኢትዮጵያውያውን ብርሃን የሚሰጥ ብቻ ሳይሆን በጎረቤት ሀገራትም የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት እንዲደርስ የሚያደርግ ነው። በዚህም ግድቡ ከኢትዮጵያ ባለፈ የቀጣናዊ ኃይል ትስስር ማእከል እንዲሁም የቱሪስት መዳረሻ በመሆን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ተናግራለች። ሲኤን ኤን በዘገባው ላይ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ክፍሌ ሆሮን በማቅረብ ኢትዮጵያ የታችኛውን ተፋሰስ ሀገራት በማይጎዳ መልኩ ግድቡን እየተጠቀመች መሆኑን አመላክቷል። ግብፅ በግድቡ ምክንያት የሚደርሳት ውሃ ቀንሷል በሚል የምታቀርበው ክስ መሰረተ ቢስ መሆኑንም ኢንጂነር ክፍሌ አስረድተዋል፡፡ አሁን ላይ በሕዳሴ ግድቡ የሚገኙ 13 ተርባይኖች በሚያመነጩት ሀይል 6 ሚሊየን ኢትዮጵያውያን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ግድቡ ከኢትዮጵያ አልፎ ሱዳን፣ ጅቡቲ፣ ኬንያ እና ታንዛኒያ ሀይል ተደራሽ ማድረግ መቻሉን፣ በቀጣይ ደግሞ ለሶማሊያ እና ደቡብ ሱዳን ሀይል ለመሸጥ ዝግጅት መደረጉን አመላክተዋል፡፡ በተጨማሪም በሕዳሴ ግድቡ በተፈጠረው ንጋት ኃይቅ ላይ የተፈጠሩት ደሴቶች ለቱሪስት መስህብነት ትልቅ አቅም መሆናቸውን በማንሳት ፤ በቀጣይም ለቱሪስት መዳረሻነት የሚያገለግሉ መሰረተ ልማቶች እንደሚገነቡ ጠቁመዋል፡፡
በክልሉ ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል
Aug 4, 2026 178
ቡታጅራ ፤ ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ) ፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት ማምጣታቸውን የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ገለፀ። ቢሮው አንድነት ለፅዳት፣ ትጋት ለአገልግሎት፣ ውሳኔ ለልማት በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጀው የምክክር ጉባኤ በቡታጅራ ከተማ እየተካሄደ ነው።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የኢንዱስትሪ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ሀላፊ አቶ ስንታየሁ ወልደሚካኤል በወቅቱ እንዳሉት፤ በ2018 በጀት ዓመት በክልሉ ከተሞችን በማህበረሰብ ተሳትፎ በማልማት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ማሳደግ ተችሏል። በክልሉ መንግስት ለከተሞች ልማት ከመደበው በጀት ባለፈ ህብረተሰቡ ከ2 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ ማዋጣቱን ተናግረዋል። በዚህም የውስጥ ለውስጥ አስፓልትን ጨምሮ የመንገድ፣ የውሃና ሌሎች መሰረተ ልማት ስራዎች ተደራሽነትን በማስፋት የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል። ከተሞችን ውብና ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ በክልሉ ሰባት ከተሞች በሁለት ምዕራፍ 165 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የክልሉን ከተሞች የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተጀመሩ ስራዎችን ለማጠናከርና የተስተዋሉ ጉድለቶችን ለማረም የምክክር መድረኩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት አመልክተዋል። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ደሱ አበጋዝ በበኩላቸው፤ በዞኑ በበጀት ዓመቱ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ በርካታ የልማት ስራዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ስለመደረጋቸው ተናግረዋል።   ከተሞችን ውብና ፅዱ ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ በተጀመሩ ስራዎች በቡታጅራ ከተማ በመጀመሪያ ምዕራፍ እየተተገበረ ከሚገኘው 21 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ውስጥ 11 ነጥብ 26 ኪሎ ሜትር የሚሆነው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ስለመደረጉም ጠቅሰዋል። የከተማዋን የአገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን የማህበረሰቡን እርካታ ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። በምክከር መድረኩ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና የዘርፉ ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው።
የግብርና ምርትና ምርታማነት እድገት የምግብ ሉአላዊነት እንዲረጋገጥ እያስቻለ ነው
Aug 4, 2026 249
ወልቂጤ፤ ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና ምርትና ምርታማነት እድገት የምግብ ሉአላዊነት እንዲረጋገጥ እያስቻለ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ከክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ጋር በመሆን በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ እንዲሁም በቀቤና ልዩ ወረዳ ኩታ ገጠም የበቆሎ እርሻዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።   ​ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በወቅቱ እንደተናገሩት፤ በክልሉ የግብርና ሜካናይዜሽንና የኩታ ገጠም እርሻ የግብርና ምርታማነት እንዲጨምር አድርጓል ። ለዚህም ለአርሶ አደሩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችንና የግብአት አቅርቦት ተደራሽነት ላይ በቅንጅት መሰራቱን ተናግረዋል፡፡ የግብርና ምርትና ምርታማነት እያደገ በመምጣቱም የምግብ ሉአላዊነት እየተረጋገጠ እንዲመጣ እያስቻለ መሆኑን አመልክተዋል።   ይህም የአርሶ አደሩን ገቢ በማሳደግ የኢኮኖሚያዊ ሽግግርን ለማፋጠን የራሱን አቅም እየፈጠረ መሆኑን ጠቁመዋል። ​በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የግብርናና ገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር በበኩላቸው፤ በጉራጌ ዞን በአበሽጌ ወረዳ እንዲሁም በቀቤና ልዩ ወረዳ በበቆሎ ልማት የመጣው ለውጥ የአርሶ አደሩ የግብርና ሙያተኞችን ምክር የመከተል ውጤት ነው ብለዋል።   ቢሮው ምርታማነትን ለማሳደግ የኩታ ገጠም አሰራር ተግባራዊ እንዲሆን ከመድረግ ባለፈ የምርት ብክነትን የሚቀንሱ የግብርና ቴክኖሎጂዎች ጥቅም ላይ እንዲውሉ ድጋፍ ማድረጉን ተናግረዋል። የዚሁ ማሳያ የሆነው የኩታ ገጠም የበቆሎ ልማትም ሰብሉን ለመንከባከብና ዘመናዊ አመራረትን ለመተግበር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። በዘርፉ የመጣውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል እንደሚሰራም አመላክተዋል።
በአማራ ክልል የፍራፍሬ ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳደገ ነው
Aug 4, 2026 155
ደሴ ፤ ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል እየተካሄደ የሚገኘው የፍራፍሬ ልማት የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት እያሳደገ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ ገለፁ። የአማራ ክልል፣ የዞንና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች በቃሉ ወረዳ በክላስተር የለማ ፍራፍሬ ልማት ጎብኝተዋል።   የቢሮ ኃላፊው አቶ ደረጀ ማንደፍሮ እንደገለፁት፣ ክልሉ ለፍራፍሬ ልማት ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ይገኛል። ባለፉት ሰባት ዓመታትም ቡናና አቮካዶን ጨምሮ ሌሎች የፍራፍሬ አይነቶች በመመረታቸው ከፍጆታ አልፎ ለውጭ ገበያ ጭምር ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል። በክልሉ በአሁኑ ወቅት አርሶ አደሩን በማደራጀት በኩታ ገጠም የፍራፍሬ ልማት እንዲሳተፍና ምርታማነቱን እንዲያሳድግ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል።   በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም 37 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ከ26 ሚሊዮን በላይ የቡናና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች እየተተከሉ መሆኑን ገልጸዋል። በቃሉ ወረዳ በኩታ ገጠም የለማው የፍራፍሬ ችግኝም ተስፋ ሰጭና ለሌሎች አካባቢዎች ተሞክሮ የሚሆን ነው ብለዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው፣ ዞኑ ለፍራፍሬ ልማት ያለውን ምቹነት በመጠቀም የአርሶ አደሩን ገቢ ማሳደግና ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።   አርሶ አደሩን በማደራጀት በኩታ ገጠም ማንጎ፣ ፓፓያ፣ ብርቱካን፣ አቮካዶና ሌሎች ፍራፍሬዎችን በማልማት ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። በዘንድሮው አረንጓዴ አሻራም ሶስት ሺህ 700 ሄክታር መሬት በፍራፍሬ ችግኝ እየተሸፈነ እንደሚገኝ ጠቁመው አሁን ላይ መስኖን በመጠቀም በበጋ ጭምር የፍራፍሬ ችግኞችን መትከል መቻሉን ተናግረዋል። አርሶ አደሩ የፍራፍሬን ጥቅም በተግባር በማየቱ በኩታ ገጠም እየተደራጀ ማልማት ጀምሯል ያሉት ደግሞ የቃሉ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሙህዲን አህመድ ናቸው።   በዚህም በአጭር ጊዜ ምርት የሚሰጡና በሽታን የሚቋቋሙ ዝርያዎችም በመንግስት እየቀረቡላቸው ነው ብለዋል። በቃሉ ወረዳ የ033 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሙባረክ መሀመድ እንደገለጹት ፣ ፍራፍሬን በክላስተር ማልማት መቻላቸው ተጠቃሚ አድርጓቸዋል። ባለፉት ጥቂት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተከሉዋቸው የማንጎና ሙዝ ችግኞች ለገበያ በማቅረብ በዘንድሮ ዓመት ብቻ ከ70 ሺህ ብር በላይ ማግኘታቸውን ገልጸዋል።   በዘንድሮው ክረምትም ተጨማሪ 200 የማንጎ ችግኞችን መትከላቸውን ተናግረዋል። በጉብኝቱ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች፣ የአማራ ክልል ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴዎችና አባላትን ጨምሮ ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ ነው
Aug 3, 2026 437
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ መምጣቱን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) ገለጹ። የዘንድሮው "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሃሳብ የሚካሄደው የ800 ሚሊዮን የአንድ ጀምበር የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ዛሬ ሐምሌ 27/2018 ዓ.ም ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በመላ ሀገሪቱ ተካሄዷል። የፕላንና ልማት ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት አመራርና ሠራተኞች በአንድ ጀምበር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በአዲስ አዳማ ፈጣን መንገድ ዳርቻ የአረንጓዴ ዐሻራቸውን አኑረዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን በመቋቋምና የአፈርና የውሃ ሀብት ጥበቃን በማጠናከር ዘርፈ ብዙ የኢኮኖሚ ፋይዳ እያስገኘ ነው።   ይህም የኃይል ማመንጫ ግድቦችን ለደለል ተጋላጭነት ከመቀነስ ባለፈ የኤሌክትሪክ ኃይልን ዘላቂነትና የምግብ ዋስትናን የሚያጠናክር አቅም እየፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል። በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርም የሚኒስቴሩና ተጠሪ ተቋማት አመራርና ሠራተኞች ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞችን መትከላቸውን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩም የኢትዮጵያን የአቮካዶና ሌሎች የፍራፍሬ ምርቶች ወጪ ንግድ ምርታማነትን በማሳደግ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለውጭ ምንዛሬ ግኝት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል።   የዜጎችን የይቻላል መንፈስ በማጎልበትም ኢትዮጵያ በአፍሪካና በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና እያተረፈች መሆኗን ገልጸዋል። የሕዝቡ ከፍተኛ ተሳትፎም አብሮነትና አንድነትን በማጠናከር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የሀገራዊ የልማት ባህል እንዲሆን እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ መምጣቱንም አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ጀሚላ መሀመድ በበኩላቸው፤ በዛሬው ዕለት በሚኒስቴሩና ተጠሪ ተቋማቱ የተተከሉት የፍራፍሬ ችግኞች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ናቸው ብለዋል።   ህብረተሰቡ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ለታቀደው ግብ ስኬት ችግኞችን በመትከልና በመንከባከብ የበኩሉን ሚና እንዲወጣም ጥሪ አቅርበዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ ነው
Aug 3, 2026 328
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ዕድገትና ለካርበን ልቀት መቀነስ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታዎች ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ሚኒስቴርና የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ከተጠሪ ተቋማቱ ጋር በመሆን በአንድ ጀምበር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር አሻራቸውን አኑረዋል፡፡ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ስለሺ ግርማ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ችግኝ መትከል ለቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት መሠረት መጣል ነው፡፡   በዱር እንስሳት ጥበቃ ስፍራዎችና በብሔራዊ ፓርኮች ውስጥ ያለውን የደን ሽፋን እንዲጨምር በማድረግ በኩል ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡ መርሃ ግብሩ የዱር እንስሳትን ስደት ከመቀነስ ባሻገር የፓርኮችን የቱሪስት መስህብነት በከፍተኛ ደረጃ በማሳደግ ጎብኚዎች ከተፈጥሮ ጋር የሚገናኙበትን፣ ንጹህ አየርና አረንጓዴ አካባቢን የሚመርጡበትን የዘላቂ ቱሪዝም ዕድል ያሰፋል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የምታሳየው የተግባር ምላሽ ዓለም አቀፍ ገጽታዋን በበጎ በመቀየር በዘላቂና በአረንጓዴ ቱሪዝም አርአያ እንድትሆን ማስቻሉን ገልጸዋል፡፡ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሀሰን መሀመድ በበኩላቸው፤ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያውያንን አንድነት በተግባር ያሳየበት ታሪካዊ ክስተት ነው ብለዋል፡፡   በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመረው ይህ ንቅናቄ ኢትዮጵያን በአየር ንብረት ጥበቃ አርዓያ እና የዓለም አቀፍ የችግሮች መፍትሄ አካል ያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የካርበን ልቀትን መቀነስ ቀዳሚ ግቡ መሆኑን በማንሳት፤ አረንጓዴ ዐሻራ በአንድ በኩል የምድርን ጸጋ መጠበቅ በሌላ በኩል ደግሞ የአየር ብክለትን የመከላከል ሚና እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት የተተከሉ የቡና፣ አቮካዶ እና የፍራፍሬ ችግኞች ለቤተሰብ የገቢ ምንጭ፣ ለሀገር ደግሞ የውጭ ምንዛሬ መሳቢያ መሆን ጀምረዋል ብለዋል፡፡ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል፣ የበረሃማነት መስፋፋት በመግታትና እና ለውሃ እጥረት ምላሽ በመስጠት ለነገው ትውልድ የተሻለች ሀገር ማስረከብም እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እያነጸ ይገኛል 
Aug 3, 2026 259
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ በጽኑ መሠረት ላይ እያነጸ እንደሚገኝ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። በአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ሀገራዊ ግብ ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በይፋ እየተካሄደ ይገኛል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር አመራሮች እና ሠራተኞች “ተስፋን እንትከል” በሚል መሪ ሐሳብ በቢሾፍቱ ፈጣን መንገድ ላይ ችግኞችን ተክለዋል።   በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት ሚኒስትሩ አለሙ ስሜ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ መርሃ ግብሩ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከልና በሀገሪቱ የተዘረጋውን የአረንጓዴ ትራንስፖርት ስትራቴጂ ለማገዝ ከፍተኛ ሚና አለው። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር የአፈር መሸርሸርን ለመከላከል፣ የውሃ ሀብትን ለመጠበቅ እና ለተተኪው ትውልድ የሚተርፍ የተፈጥሮ ፀጋን ለማስረከብ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ሰባት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የተተከሉ ችግኞች የደን ሽፋን ከመጨመር ባሻገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረጉ ሥራዎች ላይ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙ አውስተዋል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በከተሞች አካባቢ ደንን ማስፋፋት የከተሞችን ሙቀት በመቀነስ ሰዎች በእግር ወይም በብስክሌት በቀላሉ እንዲንቀሳቀሱ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር አብራርተዋል። ኢትዮጵያ ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የምታደርገውን ሽግግር በዋናነት የምትደግፈው በኤሌክትሪክ ኃይል በመሆኑ፣ የአረንጓዴ አሻራ እንቅስቃሴ የዝናብ ዑደትንና የግድቦችን ደህንነት በመጠበቅ አስተማማኝ ንጹህ ኃይል እንዲኖር እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡ መርሃ-ግብሩ ሀገሪቱ የያዘችውን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ በጽኑ መሠረት ላይ የሚጥል መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍራኦል ጣፋ ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለችው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋምና ምርታማነትን ለማሳደግ ጉልህ ድርሻ እንዳለው ገልፀዋል።   ባለሥልጣኑ ከዚህ ቀደም የተተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ የተሻለ የጽድቀት ምጣኔ እንዲኖር ሲሰራ መቆየቱንና ይህንን ተግባር አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ ሲቪል አቬሽን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ዮሐንስ አበራ በበኩላቸው ዓለም በካርበን ልቀት ምክንያት እየተፈተነች እንደምትገኝ ገልፀው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ይህንን ለመከላከል አይነተኛ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   የፐብሊክ ሰርቪስ ትራንስፖርት ዋና ዳይሬክተር አስካለ ተክሌ በበኩላቸው፤ በትራንስፖርት ዘርፉ የበካይ ጋዝ ልቀትን ለመከላከል በመርሃ ግብሩ ተሳታፊ በመሆን ችግኝ መትከል ብቻ ሳይሆን ተከታትሎ የመንከባከብ ስራም እያከናወንን እንገኛለን ብለዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ ፅዱና ማራኪ ከተሞችን በመፍጠር ለነዋሪዎች ምቹ የከተሜነት ምህዳር እየገነባ ነው
Aug 3, 2026 280
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ፅዱና ማራኪ ከተሞችን በመፍጠር ለነዋሪዎች ምቹ የከተሜነት ምህዳር እየገነባ መሆኑን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ፡፡ "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሐሳብ የሚካሄደው የአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኝ ተከላ ሀገራዊ መርሃ ግብር ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በመላ ሀገሪቱ እየተካሄደ ይገኛል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማትም በዚሁ ሀገራዊ መርሃ ግብር በመሳተፍ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ አካሂደዋል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በዚሁ ወቅት፤ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአብሮነትን መንፈስ በማጠናከር፣ ሀገረ መንግሥትን በመገንባትና የዜጎችን የኑሮ ደረጃ በማሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል።   መንግሥት የሕዝብን ተሳትፎ በማሳደግ የሚተከሉ ችግኞችን ከመትከል ባለፈ በአግባቡ በመንከባከብ እስከ ፍሬ እንዲደርሱ በትኩረት እየሠራ መሆኑንም ገልጸዋል። የከተማ ልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራምም የከተማ ግብርናን በማስፋፋት፣ የአካባቢ ጥበቃና ውበትን በማጎልበት፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠርና የኑሮ ደረጃቸውን በማሻሻል ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ከተሞች የመኖሪያ ስፍራ ብቻ ሳይሆኑ የምርት ማዕከላት እንዲሆኑ ታስቦ የተነደፈው ፕሮግራም የተተከሉ ችግኞችን ከመንከባከብ ጀምሮ ለምርት እስኪደርሱ ድረስ ክትትል የሚደረግበት መሆኑንም አብራርተዋል። አረንጓዴ ልማቶች የዜጎችን ተጨማሪ ገቢ ከማሳደግ ባለፈ፣ ከተሞችን ምቹ፣ ንጹሕና አረንጓዴ በማድረግ ለቀጣይ ትውልድ ተስማሚ የኑሮ አካባቢ ለመፍጠር ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ አስረድተዋል።
በካፋ ዞን የሻይ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በይፋ ተጀመረ
Aug 3, 2026 238
ካፋ፤ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በካፋ ዞን የሻይ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በዛሬው ዕለት በይፋ ተጀመረ። የሻይ ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በካፋ ዞን ሺሾ እንዴ ወረዳ ዋና ቦላ ቀበሌ በዛሬው እለት ተከናውኗል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ፤ የሻይ ልማትን ለማስፋት የተያዘውን እቅድ መሰረት በማድረግ በዞኑ አራት ወረዳዎች ችግኝ የማዘጋጀት ስራ ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል።   በመሆኑም በአራት የችግኝ ጣቢያዎች 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን የሻይ ችግኞች መዘጋጀታቸውን አንስተው የመትከል ስራው በዛሬው እለት በይፋ መጀመሩን ተናግረዋል። በዚሁ መሰረትም ከዛሬ ጀምሮ በቀጣዮቹ ተከታታይ 15 ቀናት በተዘጋጀው 110 ሄክታር መሬት ላይ የመትከል ስራው የሚከናወን መሆኑን ገልጸዋል። የሺሾ-እንዴ ወረዳ ግብርና አካባቢ ጥበቃና ሕብረት ስራ ልማት ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አዱኛ አለሙ፤ በበኩላቸው በወረዳው የአየር ንብረት ለውጥን ከመቋቋም በተጨማሪ ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬና የውጭ ምንዛሬን ለማያስገኙ ለቡናና ሻይ ችግኞች ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል።   ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ከአረንጓዴ አሻራ ኢንሼቲቭ ጋር በማያያዝ የሻይ ችግኞችን በማዘጋጀት በዛሬው እለት በዋና ቦላ ቀበሌ ተከላ መጀመሩን ገልጸዋል። በወረዳው 43 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ለሻይ ልማት መዘጋጀቱን ጠቅሰው የችግኝ ተከላው ይቀጥላል ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ማስጀመሪያ ለይ የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ባለሥልጣን ከፍተኛ ባለሙያ አቶ ካሳሁን ታዬ፤ በክልሉ በዘንድሮው ዓመት ለሻይ ልማት ልዩ ትኩረት በመስጠት የተሟላ ዝግጅት በማድረግ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል። በተያዘው እቅድ መሰረትም ዘንድሮ የሻይ ችግኝ ተከላ በብዛት የሚከናወን ይሆናል ብለዋል።   ከዋና ቦላ ቀበሌ ነዋሪዎች መካከል አርሶ አደር ጌታቸው ወልደጊዮርጊስ እና አቶ ንጉሴ ገብረሚካኤል የልማት ስራው በብዙ መልኩ ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል።
ዛሬ የተከልናቸው የፍራፍሬ ችግኞች አማራጭ ገቢ የሚያስገኙልን ናቸው
Aug 3, 2026 246
አዋሽ መልካሳ፤ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦በዛሬው ዕለት በአንድ ጀምበር በተካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃግብር የተተከሉት የፍራፍሬ ችግኞች፣ ከመደበኛው ግብርና ጎን ለጎን ለአርሶ አደሩ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንደሚሆኑ በአዋሽ መልካሳ የመርሃግብሩ ተሳታፊዎች ገለጹ። በመርሃ ግብሩ ላይ ከተሳተፉት መካከል ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት አቶ ቱጂ አብዶ፣ የፍራፍሬ ችግኝ ተከላ ለትውልድ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። በተለይም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር እንደሚረዳ የጠቆሙት አቶ ቱጂ፣ ሥራው ለራሳችን፣ ለክልላችንም ሆነ ለሀገራችን የሚጠቅም ነው ሲሉ ገልጸዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርና የፍራፍሬ ችግኝ ተከላው ለነገው ትውልድ ስንቅ እንደሚሆን አንስተው፤ ችግኞቹን ከመትከል ባለፈ ተንከባክበው ለፍሬ እንደሚያበቋቸው ገልጸዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ አመለወርቅ አያሌው በበኩላቸው፣ ዛሬ የተከሉት ችግኝ ለነገው ትውልድ ተስፋ እንዲሆን በማሰብ መሆኑን ገልጸዋል። ወይዘሮ አመለወርቅ አክለውም በየዓመቱ መርሃ ግብሩ ላይ መሳተፋቸውን ጠቅሰው፣ባለፉት አራት ዓመታት በተካሄዱት የተከላ መርሃ ግብሮች በመሳተፍ የተተከሉትን ችግኞች በመንከባከብ ውጤታማ ማድረግ መቻላቸውንም ገልጸዋል። የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ሳይንሳዊ ይዘቱን ተከትሎ እንዲከናወን በተሰጠው ግንዛቤ መሠረት እየተገበሩ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ አቶ አብደላ ከድር ናቸው። ችግኞችን መትከል ብቻ ሳይሆን በዘላቂነት በመንከባከብ ለውጤት ማብቃት እንደሚገባ ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ መተላለፉንም ገልጸዋል። በተለይም የአቮካዶ፣ የማንጎ፣ የፓፓያ፣ የሎሚ፣ የብርቱካንና የዘይቱን ችግኞች በስፋት መተከላቸውን ገልጸው፤ ይህም አርሶ አደሩ ከመደበኛ የሰብል ልማት ጎን ለጎን ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኝ የሚያስችለው መሆኑን ተናግረዋል። ይህም በምግብ ራስን ለመቻልና ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት ቁልፍ አጋዥ መሆኑን አስረድተዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አለሙ ቂልጡ በበኩላቸው፣ በዘንድሮው የክረምት ወቅት ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞች በ100 ሄክታር መሬት ላይ በክላስተር መተከላቸውን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ የፍራፍሬ ችግኞች የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የኑሮ ውድነትን ለመቋቋምና የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ወሳኝ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በተጨማሪም ችግኞቹ የአርሶ አደሩን ሕይወት ለማሻሻልና ገቢውን ለማሳደግ የሚያስችሉ መሆናቸውን የጠቆሙት አቶ አለሙ፤ ይህም አርሶ አደሩ ገበያ ተኮር በሆኑ የግብርና ምርቶች ላይ በስፋት እንዲሰማራ በማድረግ ዘላቂ ለውጥ ለማምጣት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ የተሻለ ምርት የሚሰጡ የአቮካዶ፣ የሎሚና የብርቱካን ምርጥ ዘሮችን ከውጭ በማስገባት ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጋቸውን አክለው ገልጸዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ለምለሚቷን ኢትዮጵያ ለመጪው ትውልድ የምናስረክብበት ትልቅ ተስፋ ነው 
Aug 3, 2026 291
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 27/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ለምለሚቷን ኢትዮጵያ ለመጪው ትውልድ የምናስረክብበት ታላቅ ተስፋ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ በአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ሀገራዊ ግብ ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በይፋ የተጀመረ ሲሆን፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ አሻራቸውን አሳርፈዋል።   ከንቲባዋ በዚህ ወቅት ባደረጉት ንግግር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ለምለሚቷን ኢትዮጵያ ለመጪው ትውልድ የምናስረክብበት ትልቅ ተስፋ ነው ብለዋል። ዛሬ ለምለም ኢትዮጵያን ለመገንባት በእጆቻችን ዝቅ ብለን የምንትክልበት፣ በሐሳብ አንድ ሆነን በተግባር ሀገራችንን በአረንጓዴ የምናልብስበት መርሃ ግብር ነው ብለዋል፡፡ በዚህ መርሃ ግብር እየተከልን ያለነው ምግባችንን፣ ጥላችንን እና ውበታችንን ነው ያሉት ከንቲባዋ፤ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚመጡ ተግዳሮቶችን ለመከላከል ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው አብራርተዋል፡፡   በሀገራችን ባለፉት ሰባት ዓመታት 48 ቢሊዮን ችግኞች መተከላቸውን ያነሱት ከንቲባ አዳነች፤ ይህም በጋራ እና በትብብር የሰራነው የዘመናችን ታላቅ ውርስ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም በከተማ አስተዳደሩ የሚገኙ ሁሉም የማህበረሰብ ክፍሎች በጋራ በመሆን በተዘጋጁ ቦታዎች ላይ ችግኞችን እየተከሉ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ የተተከሉትን ችግኞች በአግባቡ መንከባከብና መከታተል እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
ዛፍ ተስፋ ነው፤እየተከልን ያለነው ነገን እና የልጆቻችንን መጻኢ ዕድል ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Aug 3, 2026 298
አዲስ አበባ ፤ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦ዛፍ ተስፋ ነው፤ እየተከልን ያለነው ነገን እና የልጆቻችንን መጻኢ ዕድል ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከማለዳው ጀምሮ በነቃ ተሳትፎ በመረባረብ በአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል መርሐ-ግብር እያካሄደ ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለአንድ ጀምበር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (ኤ አይ) ዩኒቨርሲቲ በመገኘት የአረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ያለማቋረጥ ክረምቱን በሙሉ ዛፍ በመትከል ኢትዮጵያን የማልበስ እና ዘላቂ ለውጥ የማምጣት ጥረት ሲያደርግ መቆየቱን አስታውሰዋል። የዚህ ሀገራዊ ጥረት ዋነኛ ዓላማም ኢትዮጵያ እንድትበለፅግ፣ እንድትበራ፣ እንድትለወጥ፣ እንድታድግ እና እንድትሰለጥን ያለውን ትልቅ ሕልምና መሻት እውን ማድረግ እንደሆነ ገልጸዋል።   እንዲህ ዓይነቱ ትልቅ ሀገራዊ ሕልም ሊሳካ የሚችለው አስተማማኝ መሠረት ሲጣል ብቻ መሆኑን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በስነ-ምህዳር በኩል መሠረት መጣል ማለት አፈርን፣ ውሃን እና ተራራን መጠበቅ እንደሆነ አብራርተዋል። እየተከናወነ ያለው የችግኝ ተከላ ሥራ ለነገው ትውልድና ለልጆች የሚደረግ ኢንቨስትመንት መሆኑን የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ "እየተከልን ያለነው ተስፋን፣ ነገን እና ኢትዮጵያን ነው" ብለዋል። ይህም በትብብር እና በጋራ ጥረት የሚከናወን እንደሆነም አክለዋል። ኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃ እና በአረንጓዴ ልማት እያከናወነች ያለው ሥራ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ እውቅና ማግኘቱን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በርካታ ሀገራት የኢትዮጵያን አርአያነት እና አካሄድ ለመከተል ጥረት እያደረጉ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በዚህም ምክንያት የዓለም መንግሥታት የኢትዮጵያን ጥረት እውቅና በመስጠት፣የሽልማት አሰጣጥ ብቻ ሳይሆን ዓለም አቀፉን የአየር ንብረት ጉባኤ (COP 32) ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ መወሰናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የኮፕ ጉባኤ በዓለም ደረጃ አካባቢ ጥበቃን በተመለከተ ከ80 ሺህ እስከ 100 ሺህ የሚደርሱ ተሳታፊዎች እና ቢያንስ እስከ 100 የሚደርሱ የሀገራት መሪዎች የሚታደሙበት ትልቁ ስብሰባ መሆኑን አብራርተዋል። ይህንን መሰል ታላቅ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ኢትዮጵያም ሆነች ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ ሀገራት አዘጋጅተው እንደማያውቁ አስታውሰዋል። ጉባኤው ኢትዮጵያ ያማረች፣ የለበሰች፣ እያደገች ያለች እና ተስፋ ያላትን ገጽታዋን ለዓለም የምታሳይበት፣የተጨባጭ ልምዷን የምታካፍልበት እንዲሁም በርካታ ኢኮኖሚያዊ እና ዲፕሎማሲያዊ ጥቅሞችን የምታገኝበት ትልቅ መድረክ እንደሚሆን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የኮፕ ጉባኤን ለማዘጋጀት በምታደርገው ዝግጅት ዓመቱን ሙሉ ግንባታ፣ ተከላ እና የጽዳት ሥራዎችን አጠናክራ እንደምትቀጥል ጠቅሰው፣ የተባበረ ሕዝብ ሀገር መገንባት እንደሚችል ማሳያ እንደሚሆን ተናግረዋል። "ዛፍ የምግብ፣ የጥላ፣ የውበት እንዲሁም የመሬት መሸርሸርን የሚከላከል ዘብ ነው" ብለዋል። በመሆኑም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያውያን በጀመሩት መንገድ በመተባበር የያዙትን ሀገራዊ ግብ እንዲያሳኩ ጥሪ አቅርበዋል።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአማራ ክልል ሕዝብን የልማት ጥያቄዎች በዘላቂነት ለመመለስ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Aug 1, 2026 751
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአማራ ክልል ሕዝብን የልማት ጥያቄዎች በዘላቂነት ለመመለስ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። በአማራ ክልል የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስታውቀዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን (አሚኮ) ጋር ባደረጉት ቆይታ በለውጡ ዓመታት በአማራ ክልል የተከናወኑ የልማት ስራዎችን አስመልከተው ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቆይታቸው እንደገለጹት፤ በለውጡ ማግስት ከአማራ ክልል ሕዝብ ጋር በተደረጉ ውይይቶች የፍትሐዊ ኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ጥያቄ በዋናነት ከተነሱ ጉዳዮች መካከል አንዱ ነበር። በወቅቱ የተሰበሰቡ መረጃዎችን መሠረት በማድረግ በተካሄደው ጥናትም ክልሉ የሚገባውን ያህል ተጠቃሚ እንዳልነበረ መረጋገጡንና ይህም በክልሉ ብቻ ሳይሆን በመላው ኢትዮጵያ ዘላቂ እድገትን ማረጋገጥ ላይ ማነቆ እንደነበር አብራርተዋል። ባለፉት ዓመታት የሕዝቡን የልማት ጥያቄዎች በዘላቂነት ለመመለስ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው ለአብነትም ለ18 ዓመታት ግንባታው ሳይጠናቀቅ የቆየውን የመገጭ የመስኖ ፕሮጀክት በርካታ ሀብት በመመደብ ግንባታውን ወደ መገባደድ ማድረስ መቻሉን ተናግረዋል። በተጨማሪም ለግድቦች ግንባታ በቢሊዮኖች የሚቆጠር ገንዘብ በመመደብ ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸውን አክለዋል። በግብርናው ዘርፍ በለውጡ ማግስት 90 ሚሊዮን ኩንታል ገደማ የነበረው የክልሉ ዓመታዊ ምርት፣ ምርታማነትን ለማሳደግ በተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ ስራዎች አሁን ላይ ከ205 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ማድረስ መቻሉን ጠቁመዋል። በኢንዱስትሪው ዘርፍ ደግሞ ከለውጡ በኋላ የባሕር ዳር፣ የደብረ ብርሃን እና የአረርቲ ኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ የጣና በለስ ስኳር ፋብሪካ፣ የለሚ ሲሚንቶ ፋብሪካ እንዲሁም በርካታ ሌሎች ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ መግባታቸውን ነው ያብራሩት። ከቱሪዝም አንጻርም የላሊበላ እና የአጼ ፋሲለደስ ቤተ መንግስት እድሳቶች፣ የሎጎ ሐይቅ እና የፈለገ ግዮን ሪዞርት እንዲሁም የጎርጎራ ፕሮጀክት በቱሪዝም ዘርፍ የክልሉን ተጠቃሚነት ያሳደጉ ዋና ዋና ስራዎች መካከል ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። የመሠረተ ልማት ግንባታን በተመለከተም የነበረው 2000 ኪሎ ሜትር የመንገድ ሽፋን አሁን ወደ 4ሺህ 500 ኪሎ ሜትር ማደጉን አንስተዋል። የባሕር ዳር እና የኮምቦልቻ የአየር መንገድ ተርሚናሎችን ጨምሮ በትራንስፖርት ዘርፉ የተለያዩ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም በክልሉ የኤሌክትሪክ ሽፋን ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት ከነበረበት 20 በመቶ ወደ 40 በመቶ ሽፋን ማሳደግ መቻሉን ጠቁመው ይህ በቂ ባለመሆኑ በቀጣይ የበለጠ ይሰራል ነው ያሉት። በኮሪደር ልማት ፕሮጀክትም እንዲሁ በክልሉ በሚገኙ 32 ከተሞች በተሰራ የኮሪደር ልማት የከተሞቹ ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለስራ ዕድል ፈጠራ እና የአኗኗር ዘይቤ እንዲቀየር አስችሏል ነው ያሉት በማብራሪያቸው። በዲጂታል ኢኮኖሚው ዘርፍም በ«አምስት ሚሊዮን ኮደርስ» ኢኒሼቲቭ አማካኝነት በክልሉ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዜጎችን ማሰልጠን መቻሉንም ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ባለፉት ዓመታት ልዩ ልዩ ፈተናዎችና እንቅፋቶች ቢኖሩም በክልሉ በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በቱሪዝም፣ በዲጂታል ኢኮኖሚ፣ በመሰረተ ልማት፣ በትምህርት፣ በጤና እና በመጠጥ ውሃ ዘርፎች አመርቂ ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል። በክልሉ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን አጠናክሮ በመቀጠል የሕዝቡ የመልማትና የመጠቀም ጥያቄዎች በተሟላ ሁኔታ ምላሽ ለመስጠት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ENA
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ለህብረተሰቡ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚያችሉትን ተግባራት እያከናወነ ነው
Aug 1, 2026 570
ሀረር፤ ሐምሌ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ለህብረተሰቡ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉትን ተግባራት እያከናወነ መሆኑን አስታወቀ። በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሐረሪ ሪጅን ጽህፈት ቤት ዘመናዊ ህንጻ ግንባታ ማስጀመርያ ስነ ስርዓት አካሂዷል። በግንባታ ማስጀመሪያው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ተወካይ ለምለም ምስጋናው፣ የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈጻሚ ብርጋድየር ጀነራል ኢንጂነር ሰጠኝ ሊኪሳ እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል። ለምለም ምስጋናው በወቅቱ እንደገለጹት ተቋሙ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና አስተማማኝ አገልግሎት ለመስጠት እየተጋ ነው ። ለዚህም የተለያዩ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ጠቁመው በሐረሪ ክልል የሚገነባው ህንጻም የአገልግሎት አሰጣጡን ይበልጥ የሚያጎለብት መሆኑን አመላክተዋል። አዲስ የሚገነባው የሐረሪ ሪጅን ጽህፈት ቤትም 10 ወለሎች ያሉትና 2 ቢሊየን በሚጠጋ ብር የሚገነባ መሆኑን ተናግረዋል ። የግንባታ ስራው በ900 ቀናት እንደሚጠናቀቅ ጠቁመው፤ የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ግንባታውን እንደሚያከናውንም አስታውቀዋል። የህንጻው መገንባት በሪጅኑ የሚሰጠውን አገልግሎት ወደተሻለ ደረጃ ከፍ እንዲል ያስችለዋል ያሉት ደግሞ የአገልግሎትቱ የሐረሪ ሪጅን ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዳይሪክተር አቶ ካሊድ ጠሃ ናቸው። የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈጻሚ ብርጋድየር ጀነራል ኢንጂነር ሰጠኝ ሊኪሳ በበኩላቸው ኢንተርፕራይዙ በሀገሪቱ በርካታ የህንጻ፣ የመንገድና ሌሎች ግንባታዎችን እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል ። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሐረሪ ሪጅን ጽህፈት ቤት ዘመናዊ ህንጻ ግንባታንም በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ በፍጥነትና በጥራት እንደሚያከናውን አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም እና የመሠረተ-ልማት ግንባታዎች ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ማዕከል አድርገዋታል
Aug 1, 2026 574
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም እና የመሠረተ-ልማት ግንባታዎች ሀገሪቷን ተመራጭ ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ማዕከል እንዳደረጓት የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁ የህንድና የፊንላንድ አምባሳደሮች ገለጹ። አምባሳደሮቹ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤን ጨምሮ በዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ላይ እያከናወነቻቸው ያሉትን እርምጃዎች አድንቀዋል። የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁት በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የኢትዮጵያ ቀጣይነት ያላቸው ሪፎርሞች እና ትላልቅ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች ሀገሪቱን ለዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንት ተመራጭ መዳረሻ እያደረጓት መሆኑን ገልጸዋል። በቢሾፍቱ እየተገነባ ያለው አዲሱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያን ጨምሮ የኢትዮጵያ ፈጣን የከተሞች ለውጥ እና ትላልቅ የመሠረተ ልማት ዝርጋታዎች የውጭ ኢንቨስትመንት የመሳብ አቅሟን የሚያሳድጉ መሆኑንም አንስተዋል። ኢትዮጵያ የዲጂታል ዘርፉን ጨምሮ የኢንቨስትመንት ምህዳሩን ለማስፋት ያከናወነቻቸው ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን ነው አምባሳደሩ የጠቀሱት። ለአብነትም በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ ሰው ሰራሽ አስተውሎት እና በፋይናንስ ቴክኖሎጂ ዘርፎች በኢትዮጵያ ትልቅ አቅም መፈጠሩንም አመልክተው፤ ሪፎርሙን ጨምሮ በኢትዮጵያ የተፈጠረው ምቹ የኢንቨስትመንት ምህዳር የህንድ ኩባንያዎችን እየሳበ መሆኑንም አስረድተዋል። አዳዲስ የህንድ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ በሂደት ላይ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ከራሷ አልፎ ለቀጣናው ሰላምና መረጋጋት እየተጫወተች ያለችውን ሚናም አድንቀዋል። በኢትዮጵያ የተካሄደው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ እና የሕዝቡ ተሳትፎ የኢትዮጵያን የዴሞክራሲ ስኬታማ ጉዞ ያንጸባረቀ መሆኑን አመልክተው፤ ችግሮችን በውይይት ለመፍታት ተግባራዊ መደረግ የተጀመረው ሀገራዊ ምክክርም ትልቅ እርምጃ መሆኑን ተናግረዋል። ሂደቱ ኢትዮጵያ ልዩነቶችን እየፈታች ብሔራዊ አንድነቷን ለማስጠበቅ እና የልማት ጎዳናዋን ለማስቀጠል ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁት የፊንላንድ አምባሳደር ሲኒካ አንቲላ በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ በየዘርፉ እየታየ ያለው ለውጥ አስደማሚ መሆኑን ገልጸዋል። ፊንላንድና ኢትዮጵያ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በፈጠራ ሥራዎች እና በቴክኖሎጂ ትብብራቸውን ለማጠናከር ሰፋፊ ዕድሎች እንዳሏቸው አብራርተው፤ በልማት ትብብር በጋራ መሥራታቸውንም ይቀጥላሉ ብለዋል። ፊንላንድ ከኢትዮጵያ ጋር በንግድ እና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረቱ ኢንቨስትመንቶች ላይ ያላትን አጋርነት እንደምታጠናክርም አረጋግጠዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኢትዮጵያ የቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪውን በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል
Aug 1, 2026 559
ሆሳዕና፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲቲዩት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪውን በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን ገለፀ። የቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ኢንስቲትዩት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገቡ ተስፋ ሰጪ ውጤቶችንና የወደፊት እቅዶችን በሆሳዕና ከተማ እያገመገመ ነው። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ነጋሽ እንደተናገሩት፤ መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉ የሰጠው ትኩረት ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለማድረግ አስተዋፅዖ እያበረከተ ይገኛል።   በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኢትዮጵያን የቱሪዝም ሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪ በመደገፍ በኩል ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን አስተማማኝና ዘላቂ የኢኮኖሚ መሰረት ከማድረግ ባለፈ ለስራ ፈጠራ እንዲውል እየተሰራ መሆኑን ነው ያብራሩት። በአሁኑ ወቅትም የቱሪስት መስሕቦችን የማደስ፣ አዳዲስ የቱሪዝም መሰረተ ልማቶችን የማስፋፋት ስራ መከናወኑ የኢትዮጵያን የኮንፍረንስ ቱሪዝም ተመራጭነት እያሳደገ ነው ይህም የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች ቁጥር እንዲጨምር አድርጓል ነው ያሉት። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ1 ነጥብ 4 ሚሊየን በላይ የውጭ ጎብኚዎች እንዲሁም ከ 50 ሚሊየን በላይ የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች የተለያዩ መስሕቦችን መጎብኘታቸውን አስታውቀዋል። ኢንስቲትዩቱ በሀገሪቱ በቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ሙያዎች ዜጎችን ዓለም አቀፍ ደረጃን በጠበቀ መልኩ በማሰልጠንና ችግር ፈቺ የጥናትና ምርምር ስራዎችን በማከናወን የበኩሉን እየተወጣ ነው ብለዋል። በሆሳዕና ከተማ ለሁለት ቀናት እየተካሔደ ባለው የምክክር መድረክ የ2019 በጀት ዓመት እቅድ ላይ ውይይት እንደሚደረግ ተገልጿል።
የአማራ ክልል ምክር ቤት ለአዲሱ በጀት ዓመት ከ402 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ በጀት መርምሮ አጸደቀ
Aug 1, 2026 375
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ የአማራ ክልል ምክር ቤት በ2019 በጀት ዓመት ለሚካሔዱ የልማት ዕቅዶች ማስፈጸሚያ የሚውል ከ402 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ በጀት መርምሮ አጽድቋል። የክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 12ኛ መደበኛ ጉባኤ በሦስተኛ ቀን ውሎው በተለያዩ አጀንዳዎች ዙሪያ በመምከር እና የአዲሱነ በጀት ዓመት የዕቅድ ማስፈጸሚያ በጀት በማጽደቅ ተጠናቋል። የክልሉ ገንዘብ ቢሮ ኃላፊ አታላይ ጥላሁን የበጀት ረቂቁን ባቀረቡበት ወቅት እንዳሉት፤ በጀቱ የክልሉን ህዝብ የመልማት ፍላጎት መሰረት ያደረገ ነው። ከበጀቱ ውስጥ ከ286 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ የሚሆነው በክልሉ ከሚሰበሰብ ገቢ የሚሸፈን ሲሆን 111 ቢሊየን የሚጠጋው ደግሞ ከፌደራል መንግስት ጥቅል የቀመር መደበኛ ድጋፍ የሚገኝ ነው ብለዋል። ቀሪው ከዘላቂ ልማት ግቦችና መሰል የፋይናንስ ምንጮች በሚገኝ ሀብት የሚሸፈን እንደሆነም ተናግረዋል።   የበጀት ድልድሉ ሊኖሩ የሚችሉ ለውጦችን፣ የመዋቅር ማሻሻያዎችን፣ ብሎም ወረዳዎችና ከተሞች የድህነት ተኮር ዘርፍ ያለባቸውን የካፒታል በጀት ውስንነት መሰረት የተደረገ ነው ብለዋል። የተመደበው በጀት ካለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀር በ176 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ወይም 78 ነጥብ 8 በመቶ ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል። በጀቱ የክልሉን ህዝብ የላቀ የልማት ጥያቄ ፍላጎት መሰረት በማድረግ የቀረበ እንደሆነም አብራርተዋል። የቀረበውን በጀት የህዝብን የልማት ጥያቄ በአግባቡ ሊመልስ በሚችል አግባብ ለታለመለት ዓላማ በቁጠባ ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ለስኬታማነቱም በየደረጃው ያለው ባለድርሻ አካል የድርሻውን መወጣት እንዳለበት አሳስበዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም