ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የቱሪዝም ትንሳኤን ያበሰረው የመደመር እሳቤ
Sep 16, 2026 299
ኢትዮጵያ አስደማሚ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ የቱሪዝም ሀብቶች ባለቤት ናት ። የጎብኚዎችን ቀልብ የሚስቡ ደጋግመው ቢያዩዋቸው ፣ ቢታደሙባቸው የማይሰለቹ ተጠንተውም የማያልቁ ፀጋዎች ቢኖሯትም ለዘመናት በወጉ ሳትገልጣቸው የሚጠበቀውን ያክልም ሳይጎበኙ ሳይተዋወቁም ቆይተዋል። ይህን ባለማድረጓ ደግሞ ከዕልፍ የቱሪዝም ጸዋጋዎቿ ሳትቋደስ ዘመናትን ተሻግራለች። “በታሪክም ሆነ በተፈጥሮ ጸጋዎች ከኛ ጋር ሊወዳደሩ የማይችሉ ብዙ ሀገራት ከኢንዱስትሪው ብዙ አትርፈዋል። እኛ ግን እንቁዎቻችንን ደብቀን ታሪካችንን አቧራ አልብሰን ለዘመናት ቆይተናል።” የመደመር መንግሥት መጽሐፍ ገጽ 259 ዛሬ ግን ይህ ታሪክ እየተቀየረ ነው። ከመደመር መንግሥት አምስት ወሳኝ የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ በሆነው ቱሪዝም ቅርሶችንና ወሳኝ ፀጋዎችን ከቁስ ወደ ቁርስ እየለወጠ፣ ኢትዮጵያን እየገለጠ እንዲመጣ እየተደረገ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአራት ኪሎ ቤተመንግስት “ሀ” ተብሎ የተጀመረው አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻ ልማት በገበታ ፕሮጀክቶች አማካኝነት ወደ ሁሉም የሃገራችን ክፍሎች ተዳርሷል። በኢትዮጵያ ትኩረት ተነፍጓቸው የነበሩት የሀገራችን የቱሪዝም ሀብቶች በመደመር መንግሥት ቅድሚያ ተሰጥቷቸው ትንሳኤያቸው ተበስሯል። ለዘመናት አቧራ ለብሰው የኖሩ ዕንቁ የቱሪዝም ሀብቶች አቧሯቸው እየተራገፈ ነው። ከዳሎል እስከ ስሜን ተራሮች ማራኪ ተፈጥሯዊ መስህቦች ይበልጥ ለዓለም እየተዋወቁ ነው። አዳዲስ ተፈጥሯዊ ፀጋዎችም በቱሪዝም ልማት ኢኒሼቲቮች የመገለጥና የመታወቅ ዕድል አግኝተዋል። የመደመር እሳቤ የምናብ ከፍታና የመፈጸም ልክ አንዱ ጉልህ ማሳያ የቱሪዝሙ ዘርፍ ፕሮጀክቶች ናቸው። ከነዚህ ኢኒሼቲቮችም መካከል አንዱ ከቤተ መንግስት እደሳት ጀምሮ አዲስ አበባን እንደ ስሟ አዲስ ያደረጋት የገበታ ለሸገር ፕሮጀክት ነው። የገበታ ለሸገር ፕሮጀክት የቱሪዝም አብዮትን በመቀስቀስ የአንድነት ፓርክን፣ እንጦጦና ወዳጅነት ፓርክና ሌሎች ተያያዥ ፕሮጀክቶችን ዕውን አድርጓል። ዛሬ ላይ አዲስ አበባን አዲስ መልክ አጎናጽፎ፤ የነተቡ ሰፈሮች ወደ ውብ መልኮች ተቀይረው የሚሊዮኖች ጎብኚዎች መዳረሻ ሆነዋል። ከገበታ ለሸገር በመቀጠል የኢትዮጵያን አዳዲስ መልኮች የገለጠው ኢኒሸቲቭ ደግሞ የገበታ ለሀገር ፕሮጀክት ነው። ገበታ ለሀገር ከኦሮሚያ ክልል የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ወንጪን፣ ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ዳውሮና ኮንታን የሸፈነው ኮይሻን፣ከአማራ ክልል የጣናን ምዕራባዊ ዳርቻ የተንተራሰችውን ጎርጎራን ውብ አድርጓል። እነዚህ ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያን አይነተ ብዙ ታሪክ፣ ተፈጥሮንና ባህል በመግለጥ ለኢትዮጵያ ተጨማሪ ሞገስና ድምቀት ሆነዋል። ከገበታ ለሀገር ቀጥሎ ገቢራዊ የተደረገው የገበታ ለትውልድ ፕሮጀክት አድማሱ በሶማሌ ክልል ሸበሌ ሪዞርትን፣ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ የደንቢ ኢኮ ሎጅን፣ በአማራ ክልል የሐይቅ ሎጎ ሪዞርትን፣ በአፋር ክልል የኒዒን ሌ ፓልም ሎጅ እንዲሁም የአርባምንጭ ኮንፈረንስ ሪዞርትን እውን አድርጓል። ከገበታ ለሸገር እስከ ገበታ ለትውልድ ፕሮጀክቶች ባሻገር የመደመር መንግስት ታሪካዊ ቅርሶችን የመጠበቅ፣ እሴት ጨምሮ የመግለጥ አኩሪ ስራዎችንም አከናውኗል። ለዚህ ደግሞ ከብሔራዊ ቤተ መንግስት ጀምሮ ጥንታዊ አብያተ መንግስታት፣ ታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቅርሶች ተጠግነዋል። የባለፉት ጥቂት ዓመታት የቱሪዝም ዘርፍ ለውጦች የኢትዮጵያን ገጽታ ያስተዋወቁ፤ በየአካባቢው ተስፋና ልማትን የፈነጠቁ፣ ዘመን ተሻጋሪ ስራዎች ናቸው። እነዚህ ፕሮጀክቶች በኢትዮጵያ የዕድገትና የብልጽግና ታሪክ ውስጥ በደማቁ የሚጻፉ አንቀጾች ሆነው ለትውልድ የተኖሩ ዓሻራዎች ናቸው።
የኢትዮጵያና እስራኤል ትብብር ወደ ላቀ ምዕራፍ ተሸጋግሯል-አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር)
Sep 16, 2026 272
አዲስ አበባ፤መስከረም 6/2019 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያና እስራኤል ሁሉን አቀፍ ትብብር መጠናከር የሀገራቱን ግንኙነት ወደ ላቀ ምዕራፍ ማሸጋገሩን በእስራኤል የኢትዮጵያ አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ገለጹ። አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤የሁለቱ አገራት ግንኙነት ጥልቅ ታሪካዊ መሠረት ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ግንኙነቱ አሁን ላይ በመንግሥታት ትብብር፣በኢንቨስትመንት፣በቴክኖሎጂ እና በሰዎች አቅም ግንባታ ላይ የተመሠረተ ሁሉን አቀፍና ዘመናዊ አጋርነት ላይ መድረሱን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ እና እስራኤል ከጥንት ጀምሮ የነበራቸው ልዩ ታሪካዊ ግንኙነት ዛሬ ለደረሰበት ጠንካራ የሁለትዮሽ አጋርነት እንዳበቃቸው ተናግረዋል። በአዲስ አበባ የሚገኘው የእስራኤል ኤምባሲ የሁለቱን አገራት የረጅም ጊዜ ግንኙነት ለማጠናከርና ለማስፋት በተለያዩ ዘርፎች በስፋት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አስረድተዋል። የሁለቱ አገራት አበይት የትብብር መስኮች አንዱ የሆነው ግብርና፤ የእስራኤል ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ኩባንያዎችን በመገንባት ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂዎችንና ባለሙያዎችን ወደ ሀገር ውስጥ እንዲያስገቡ መልካም አጋጣሚን መፍጠሩን ነው ያነሱት። የእስራኤል ኩባንያዎች በፍራፍሬና በአትክልት ልማት ላይ የተሰማሩባቸውን በቢሾፍቱ አካባቢ የሚገኙ የግብርና ስራዎች በማሳያነት ጠቅሰዋል። በዘርፉ ያለው ትብብርና ኢንቨስትመንት ኢትዮጵያ አቮካዶን ጨምሮ የግብርና ምርቶቿን ወደ አውሮፓ እና እስያ ገበያዎች የምታቀርብበትን አቅም እንዲያድግ አስተዋጽኦ አድርጓል ብለዋል አምባሳደር አብርሃም። በተጨማሪም የኢትዮጵያ ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለውጭ ባለሀብቶች፣ እስራኤላውያንን ጨምሮ ምቹ ሁኔታዎችን እየፈጠረ መሆኑን አመልክተዋል። የውጭ ባለሀብቶችን በመሳብ ረገድ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው የገለጹት አምባሳደሩ፤ የተደረጉት ማሻሻያዎች ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ስራ ለመጀመር እና የኢንቨስትመንት ዕድሎችን ለመመልከት እያገዟቸው እንደሚገኙ ተናግረዋል። የማዕድን አቅምን ጨምሮ የኢትዮጵያ ተፈጥሮ ሀብቶች ተጨማሪ የእስራኤል ኢንቨስትመንቶችን መሳብ የሚያስችሉ መሆናቸውን ነው ያስረዱት። የእስራኤል ኩባንያዎች ወርቅን ጨምሮ በተለያዩ ማዕድናት ፍለጋና ማምረት ስራዎች ላይ ተሰማርተው እንደሚገኙ ጠቁመዋል። ጤና ሁለቱ አገራት ትብብራቸውን እያሰፉባቸው ካሉ ዘርፎች መካከል አንዱ መሆኑን የገለጹት አምባሳደሩ፤ የእስራኤል ሀኪሞች ከኢትዮጵያ የህክምና ባለሙያዎች ጋር በመቀናጀት የአቅም ግንባታን ጨምሮ በተለያዩ መርሃ ግብሮች ላይ በትብብር እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ መስኮች፣በተለይም በሳይበር ደህንነት ዙሪያ ያለውን ትብብር አምባሳደሩ አንስተዋል። እስራኤል የሳይበር ደህንነት ተግዳሮቶችን በመቅረፍ ረገድ ያከማቸችውን ልምድ ለኢትዮጵያ ለማካፈል እንደምትሻም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥን የሕልውና ጥያቄ ነው
Sep 16, 2026 408
አዲስ አበባ፤ መስከረም 6/2019 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥን ጠንካራ መሰረት ያለው የሕልውና ጥያቄ መሆኑን የኢትዮጵያ ባሕር ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አብዱልበር ሸምሱ ገለጹ። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነትን በሴራ ማጣት በትራንስፖርት፣ በሎጂስቲክስና በወደብ አገልግሎት የገቢና ወጪ ንግድ ሥርዓት ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ እያደረሰ ይገኛል። በየዓመቱም በቢሊዮን የሚቆጠር የውጭ ምንዛሬ እንድትከፍል በማስገደድ በአጠቃላይ የኢኮኖሚ ዕድገትና እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያስከተለ ነው። ይህም የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት የሀገርን ተፈጥሯዊ፣ መልክዓ ምድራዊ፣ ስትራቴጂካዊና ሕጋዊ የባሕር በር ባለቤትነት ለማስመለስ ያነሱትን ጥያቄ ምክንያታዊነት ያጎላዋል። ኢንጂነር አብዱልበር ሸምሱ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በባሕር ላይ የሎጂስቲክስና ትራንስፖርት እንቅስቃሴ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብት ጠንካራ አቅም የገነባች ሀገር ናት። በባሕር ላይ የንግድ መስመር፣ የሎጂስቲክስና ትራንስፖርት እንቅስቃሴም በትላልቅ መርከቦች፣ ብቁ የመርከብ ካፒቴኖችና በዳበረ መዋቅር የሚከናወኑ ተግባራት የኢትዮጵያን አቅም የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ማጣት የሚያስቆጭ ነው ያሉት ዋና ሥራ አስፈፃሚው፤ ይህም በባሕር ላይ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ እንዳለው አንስተዋል። ኢትዮጵያ ለሺህ ዘመናት ስትጠቀምባቸው ከነበሩት የቀይ ባሕር ሉዓላዊ ወደቦቿ እንድትገለል የተፈጸመባት ታሪክ ይቅር የማይለው በደል በዘርፉ ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያሳደረባት መሆኑን ገልጸዋል። የባሕር በር አለመኖሩም ኢትዮጵያን በወደብ ኪራይ፣ በሸቀጦች የወጪና ገቢ እንቅስቃሴ መዘገየት በመፍጠርና ቀጥተኛ ተፅዕኖ በማሳደር የኢኮኖሚ ዕድገትን እየጎተተ መሆኑን አስረድተዋል። የባሕር በር ባለቤትነትም በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ የወደብ አገልግሎት የሚያጋጥሙ ተፅዕኖዎችን በማስቀረትና የኢኮኖሚ ዕድገትን በማፋጠን ለዜጎች የሕይወት መሻሻል መሠረት መሆኑን አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄም በወደብ አገልግሎት የሚያጋጥሙ የትራንዚት መጨናነቅን፣ የገቢና ወጪ ምርት መዘግየትንና የወደብ ኪራይን ለማስቀረት ጠንካራ የኢኮኖሚ መሠረት ያለው መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የኢትዮጵያን ታሪካዊ፣ ሕጋዊ፣ መልክዓ ምድራዊና ተፈጥሯዊ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥን የህልውና ጉዳይ መሆኑን አስረድተዋል። የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ በሚደረገው ጥረትም ሁሉም ዜጋ በትብብርና በንቁ ተሳትፎ የድርሻውን መወጣት እንዳለበት አስገንዝበዋል።
በባሕርዳር ከተማ ከ61 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል 
Sep 16, 2026 136
ባህር ዳር ፤መስከረም 6/2019 (ኢዜአ)፦በአዲሱ በጀት ዓመት ከ61 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር አቅዶ ወደ ሥራ መግባቱን የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ሥራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ዘመነ አሰፋ እንደገለጹት፤ ለወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር አንዱ የልማት ቁልፍ ተግባር ተደርጎ እየተሠራበት ነው። በዚህም በበጀት ዓመቱ ከ61 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ ተግባራዊ እንቅስቃሴ መጀመሩን ነው የገለጹት። የሥራ ዕድሉ በከተማ ግብርና፣ በኮንስትራክሽን፣ በእንጨትና ብረታ ብረት፣ በሌሎች ዕድገት ተኮር ዘርፎች እንዲሁም በውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት ዘርፎች መሆኑን አስረድተዋል።   የከተማ አስተዳደሩ ከአጋር ተቋማት ጋር በመተባበር ወደ ሥራ ለሚገቡ ወገኖች ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር፣ ከ230 ሄክታር በላይ መሬት፣ 124 ሼዶችና 124 ኮንቴይነሮችን ማመቻቸቱን ነው የተናገሩት። በበጀት ዓመቱ 2 ሺህ 767 አዳዲስ ኢንተርፕራይዞችን በዶሮ፣ በወተት፣ በጨርቃ ጨርቅና ሌሎች ዘርፎች በማደራጀት ወደ ሥራ ለማስገባት መታቀዱንም ጠቁመዋል። የ"እናንዬ፣ አስማረችና ጓደኞቻቸው" የዓሣ ምርት ማኅበር ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ እናንዬ ታምሩ በበኩላቸው፤ ባለፈው ዓመት 70 አባላትን በማቀፍ በዓሣ ልማት ዘርፍ ተደራጅተው ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል። ማኅበራቸው በቀን እስከ 20 ኪሎ ግራም ዓሣ በማዘጋጀትና ለገበያ በማቅረብ አባላቱን ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።   የ"አዲሴና ምሕረት" የዶሮ እርባታ ሽርክና ማኅበር ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ አዲሴ አብረሃም፤ በየዙሩ 1 ሺህ ጫጩቶችን በማስመጣትና በማሳደግ ለተጠቃሚዎች እያሰራጩ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ዘርፉ አዋጭ በመሆኑ ሌሎች ወጣቶችም ተደራጅተው ወደ ሥራ በመግባት የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ኑሮ ለመለወጥ መሥራት እንዳለባቸው ገልጸዋል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ሥራና ክህሎት መምሪያ በ2018 በጀት ዓመት ከ55 ሺህ በላይ የሥራ ዕድሎችን በመፍጠር ከዕቅድ በላይ ስኬታማ አፈጻጸም ማስመዝገቡን መግለጹ ይታወሳል።
በክልሉ በመኽር ወቅቱ በቅባትና በጥራጥሬ ሰብሎች ከለማው ማሳ ከ34 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል
Sep 16, 2026 289
ባህርዳር፤ መስከረም 6/2019 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በመኸር ወቅቱ በቅባትና በጥራጥሬ ሰብሎች ከለማው ማሳ ከ34 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ‎የቢሮው የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማንደፍሮ አስላከ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክልሉ በ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት ለውጭ ገበያና ለኢንዱስትሪ ግብዓትነት የሚሆኑ ምርቶችን በብዛትና በጥራት አምርቶ ለማቅረብ እየተሰራ ነው።   ‎ለዚህም በመኸር ወቅቱ ከአንድ ሚሊዮን ሄክታር በላይ ማሳ በሰሊጥ፣ በአኩሪ አተር እና ማሾ ሰብሎች ለምቶ እንክብካቤ እየተደረገለት መሆኑን ተናግረዋል። የኩታ ገጠም አሰራርን መሰረት አድርጎ ከለማው አጠቃላይ ማሳ ውስጥ ከግማሽ ሚሊዮን ሄክታር በላዩ በሰሊጥና ቀሪው ደግሞ በጥራጥሬ ሰብሎች የለማ መሆኑን ጠቅሰዋል። አሁን ላይ ቡቃያው በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ጠቁመው አጠቃላይ ከለማው ማሳ ከ34 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ አመላክተዋል። በሰብል አሰባሰብ ወቅት የምርት ብክነትን ለመቀነስና ጥራቱን ለመጠበቅ ለአርሶ አደሩና ለአልሚ ባለሃብቶች ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል።   ‎በምዕራብ ጎንደር ዞን የመተማ ወረዳ ነዋሪ አርሶአደር ንጉሴ አለልኝ፤ በ10 ሄክታር ማሳ ላይ ላለሙት የቅባትና የጥራጥሬ ሰብሎች እንክብካቤ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። አሁን ላይ የሰብሉ ቁመና በጥሩ የእድገት ደረጃ ላይ የሚገኝ በመሆኑ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ አመላክተዋል። በምርት ዘመኑ ስምንት ሄክታር ማሳ ላይ ሰሊጥና አኩሪ አተር ማልማታቸውን የገለፁት ደግሞ የወረዳው ነዋሪ አርሶ አደር ወለላው ላቀው ናቸው። ‎ከተያዘው ወር አጋማሽ ጀምሮ የደረሰ ሰሊጥ ስብሰባ እንደሚጀምሩም አመላክተዋል።
የግብርና ምርት እሴት ሰንሰለትን ለማሻሻል ትብብርና የፖሊሲ ማዕቀፍ መተግበር ይገባል - ኢጋድ
Sep 15, 2026 398
አዲስ አበባ፤ መስከረም 5/2019 (ኢዜአ)፡- በአባል ሀገራት ቀጣና የግብርና ምርትን ለማሻሻልና እሴት ለመጨመር ትብብርን በማጠናከርና ሊያግባባ የሚችል የጋራ የፖሊሲ ማዕቀፍ መተግበር እንደሚገባ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ገለጸ። ኢጋድ እንደ አውሮፓውያን የዘመን አቆጣጠር ከ2026 እስከ 2035 ለ10 ዓመታት የሚተገብረውን የቀጣናው የግብርና ምርት የምግብ ሥርዓት ኢንቨስትመንት ዕቅድ የባለሙያዎች ግምገማና በሚኒስትሮች የማጽደቅ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ እያካሄደ ነው። የኢጋድ የምግብ ሥርዓት ግንባታ አቅም ፕሮግራም አስተባባሪ ሰናይት ረጋሳ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የኢጋድ ቀጣና ሀገራት እንደ ጎርፍ፣ ድርቅና መሰል የተፈጥሮ አደጋዎችን በተደጋጋሚ የሚያስተናግዱ ናቸው። የአፍሪካ መሪዎች እ.ኤ.አ. በ2025 በዩጋንዳ ካምፓላ ተገናኝተው የምግብ ሥርዓት ግንባታ አቅም ስምምነት ሰነድ በመፈራረም ለትግበራው ቁርጠኝነታቸውን ማሳየታቸውን አስታውሰዋል።   በዚህም በአህጉር፣ በቀጣናና በሀገር ደረጃ ገቢራዊ ለማድረግ እንቅስቃሴ መደረጉን ገልጸው፤ የኢጋድ የግብርና ምርት የምግብ ሥርዓት ኢንቨስትመንት የ10 ዓመት ዕቅድ የዚሁ አካል መሆኑን ተናግረዋል። ከምግብ ዋስትና ጋር የተያያዙ ችግሮች በሀገር ደረጃ ብቻ የሚፈቱ አለመሆናቸውን ገልጸው፤ የ10 ዓመት ዕቅዱ የሀገራትን የጋራ ትብብር እንደሚያጠናክር ብለዋል። ለአብነት የበረሃ አንበጣ በቀጣናው ቢከሰት አንድ ሀገር ብቻውን የሚፈለገውን ውጤት ማምጣት አይችልም ያሉት አስተባባሪዋ፤ የቀጣናው ሀገራት በጋራ ጉዳዮች ላይ የጋራ መፍትሔና እርምጃ መውሰድ የሚችሉበትን ዕድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ዕቅዱ ሀገራት በተናጠል ከራሳቸው ነባራዊ ሁኔታ በመነሳት ከሚወስዷቸው የመፍትሔ አማራጮች ባለፈ ትብብራቸውን ማጠናከርና የዕውቀት ሽግግር መፍጠር እንደሚያስችልም ተናግረዋል። የኢጋድ የግብርና ምርት የምግብ ሥርዓት ኢንቨስትመንት ዕቅድ የግብርና ምርትን ከማሳደግ ባለፈ እሴት መጨመር የሚቻልበትን አቅም መገንባት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።   ድርቅ በሚከሰትበት ወቅት ቅድመ ማስጠንቀቂያ መስጠት፣ የሴቶችን ተሳትፎ ማሳደግ፣ ድንበር ተሻጋሪ በሽታዎችን በጋራ መከላከል የሚችሉበት ሥርዓት እንዲዘረጋ ድጋፍ ማድረግ ያስችላል ብለዋል። ከዚህም ባለፈ የቀጣናው ሀገራት የሚስማሙበትን እና ግብራዊ ሊያደርጉት የሚችለውን የጋራ ቀጣናዊ የፖሊሲ ማዕቀፍ እንዲኖራቸው የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ሚኒስትር ከፍተኛ አማካሪና የአፍሪካ ልማት ፕሮግራም ተወካይ ዜና ሀብተወልድ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከአፍሪካና ከቀጣናው ሀገራት ጋር የተናበበ ዕቅድ በመተግበር በአርዓያነት የሚጠቀስ ውጤት አስመዝግባለች ብለዋል። በሌማት ትሩፋት፣ በስንዴ ልማት እንዲሁም አሁን በስፋት ግብራዊ በተደረገው የሩዝ ልማት ተጨባጭ ለውጥ መገኘቱን ገልጸዋል። ግብርና የአፍሪካ የልማት ሞተር መሆኑን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ ይሄንን ታሳቢ ያደረገ የግብርና ዕመርታ አምጥታለች ብለዋል። በቀጣይም ኢትዮጵያ በካምፓላ ስምምነትና በኢጋድ የ10 ዓመት የኢንቨስትመንት ዕቅድ ላይ በመመስረት የቀጣይ 10 ዓመት የተናበበ ዕቅድ በማውጣት ግብራዊ እንደምታደርግ ገልጸዋል። ኢጋድ ኢትዮጵያን ጨምሮ ለቀጣናው ሀገራት የምግብ ዋስትና መረጋገጥና በሽታ መከላከል ሥርዓት ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸው፤ ቀጣናዊ ትብብርና ተቋማዊ አንድነትን ማጠናከር ይገባል ብለዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስትራቴጂካዊ አቅምና ሙያዊ ብቃት ለመላው አፍሪካ አርአያ የሚሆን ነው 
Sep 15, 2026 328
አዲስ አበባ፤ መስከረም 5/2019 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፉት አስርት ዓመታት የገነባው ስትራቴጂካዊ ዲሲፕሊን፣የቴክኒክ ልህቀት እና የላቀ ሙያዊ የብቃት ደረጃ ለመላው አፍሪካ አርአያ የሚሆን ነው ሲሉ የቀድሞ የአሜሪካ የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ሚኒስትር ቲቦር ናጊ ገለጹ። የአየር መንገዱ ስኬት በመንግስት ባለቤትነት ብቻ የተወሰነ ሳይሆን በሙያዊ ስነምግባርና በገለልተኝነት በመመራቱ ጭምር መሆኑን የቀድሞው ዲፕሎማት ከፐልስ ኦፍ አፍሪካ ጋር ባደረጉት ቆይታ ተናግረዋል። ተቋሙ በቴክኒክ አቅምና በሰው ኃይል ልማት ላይ ያደረገው ሰፊ ኢንቨስትመንት አሁን ላይ ለደረሰበት ዝና እና ስኬት ቁልፍ ሚና መጫወቱን አመልክተዋል።   አየር መንገዱ ጠንካራ ስትራቴጂ ያለው እና የላቀ የቴክኒክ አቅም የተጎናጸፈ መሆኑን ገልጸው የአውሮፓ አየር መንገዶች አብራሪዎቻቸውን በአዲስ አበባ በሚገኙ ማሰልጠኛዎች (ሲሚውሌተር) ልምምድ እንዲያደርጉ እንደሚልኩ አንስተዋል። የተቋሙ መካኒኮችም በዓለም ምርጥ ከሆኑት ተርታ እንደሚመደቡ ጠቅሰው መንገደኞች ሁልጊዜም የኢትዮጵያ አየር መንገድን ተመራጭ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል። ዓለም አቀፍ በረራዎች በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ምክንያት ተቋርጠው በነበሩበት አስቸጋሪ ወቅት አየር መንገዱ የላቀ ሙያዊ ብቃት ማሳየቱን ናጊ አስታውሰዋል። በወቅቱ የቀድሞ የአሜሪካ የአፍሪካ ጉዳዮች ረዳት ሚኒስትር ቲቦር ናጊ በሚያገለግሉበት ወቅት፣ ሌሎች አየር ማረፊያዎች በረራቸውን ባቋረጡበት ጊዜ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስራ መቀጠሉን ገልጸዋል። በዚህም ምክንያት አሜሪካ ዜጎቿን ከአፍሪካ ለማስወጣት አየር መንገዱን በስፋት ስትጠቀም እንደነበር በማውሳት የአየር መንገዱን ጽናትና አይበገሬነት አንስተዋል። የቢሾፍቱን ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ያደነቁ ሲሆን ኢትዮጵያ በአፍሪካ የኢኮኖሚና የአቪዬሽን መሪነት እንድትቀጥል ይህ ፕሮጀክት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።   የአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታ የረጅም ጊዜ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ አርቆ አሳቢነት የተሞላበት አካሄድ ነው ብለዋል። አዲስ አበባ እጅግ ከፍ ያለ ቦታ ላይ መሆኗ ለአንዳንድ አውሮፕላኖች ማረፍና መነሳት አስቸጋሪ መሆኑን በመጥቀስ፣ ይህም የፕሮጀክቱን ስትራቴጂካዊ ፋይዳ የጎላ የሚያደርገው መሆኑን ተናግረዋል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ፕሮጀክት 12.5 ቢሊዮን ዶላር የሚፈጅ ሲሆን፤ ይህ ሜጋ ፕሮጀክት በቢሾፍቱ ከተማ እየተገነባ ይገኛል። ፕሮጀክቱ ኢትዮጵያን ይበልጥ የአፍሪካ ግዙፍ የአቪዬሽን ማዕከል የሚያደርጋት ነው። የኢትዮጵያን አየር መንገድ ስኬት ከረጅም ጊዜ የተቋም ጽናትና ኢንቨስትመንት ጋር የሚቆራኝ ነው ብለዋል። የቴክኒክ ባለሙያዎች ብቃት፣ስትራቴጂካዊ አስተዳደር እና የመሰረተ ልማት መቀናጀት እንዲሁም የሀገሪቱ ኢኮኖሚ እና የዓለም አቀፍ ትስስር እድገት አየር መንገዱ ያለውን አህጉራዊ ሚና ይበልጥ እንደሚያሳድገው አመልክተዋል።
የስንዴ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ አርሶ አደሩን ተጠቃሚ የሚያደርግ ፕሮጀክት ተግባራዊ እየተደረገ ነው
Sep 15, 2026 271
አዳማ፤ መስከረም 5/2019 (ኢዜአ) ፡- የስንዴ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያግዝ የስንዴ ልማት እሴት ሰንሰለት ፕሮጀክት ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ ለኢዜአ እንዳስታወቀው በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም የስንዴ ልማት እሴት ሰንሰለት ፕሮጀክት ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል። ፕሮጀክቱ የስንዴ ሰብሉ ድርቅን፣ ከፍተኛ ሙቀትን፣ ተባዮችንና ያልተጠበቀ የዝናብ መዛባትን የሚቋቋሙ የምርጥ ዘር ዝርያዎችን መጠቀም ላይ እንደሚያተኩርም ተገልጿል። በፕሮጀክቱ በስንዴ ልማቱ ላይ የሚካሄዱት የድጋፍና ክትትል ተግባራቱ በምርት ላይ ብቻ የተወሰኑ ሳይሆኑ ሙሉ የልማት የእሴት ሰንሰለቱን የሚያካትት መሆኑም እንዲሁ። ይህ አሰራር ለገበሬዎች ከዘርና ቴክኖሎጂ አቅርቦት ጀምሮ እስከ ሰብል ስብሰባ፣ ማከማቸት፣ ማቀናበርና ምርቱን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እስከ ማቅረብ ያሉትን ሙሉ ሂደቶች ያቃልላል ተብሏል። በአጠቃላይ ሀገሪቱ የአየር ንብረት ለውጥ በሚያመጣው ተጽዕኖ ሳትበገር የስንዴ ምርቷን በማሳደግ የምግብ ዋስትናዋን ለማረጋገጥና ወደ ውጭ የመላክ አቅሟን ለማጠናከር እያደረገች ያለችውን የተቀናጀ እንቅስቃሴ የሚደግፍ ፕሮጀክት መሆኑ ነው የተገለጸው። በግብርና ሚኒስቴር የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ አብዱልሰመድ አብዶ ለኢዜአ እንዳስታወቁት ፕሮጀክቱ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ ሶማሌ እና አፋር ክልሎች ነው። በዚህም በክልሎቹ የሚገኙ 76 ወረዳዎችና 1 ሺህ 129 ቀበሌዎችን በፕሮጀክቱ ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ለአምስት አመታት ተግባራዊ በሚደረገው በዚህ ፕሮጀክት በአካባቢዎቹ የስንዴ ምርትና ምርታማነትን በማሻሻል አነስተኛ ይዞታ ያላቸው ስንዴ አምራች አርሶ አደሮችን ገቢ ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህ ረገድ እየተከናወኑ ካሉ ስራዎች መካከል የዘር ግብዓት አቅርቦት ዋነኛው መሆኑን ጠቅሰው ለዚህም በየደረጃው ከሚገኙ የግብርና ምርምር ተቋማት ጋር በመቀናጀት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ፕሮጀክቱ ተግባራዊ በተደረገባቸው ባለፉት ሁለት አመታት ውስጥ የዳቦና የመኮሮኒ ስንዴ ዘርን በጥራት በማምረት በፕሮጀክቱ ለታቀፉ አርሶ አደሮች ማሰራጨት መቻሉን ገልጸዋል። ይህም የመነሻ ዘር አቅርቦት ከማሻሻል ባለፈ የስንዴ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ማስቻሉን አመላክተዋል። ፕሮጀክቱ ከአፈር ለምነትና ጤንነት ጋር ተያይዞ ስንዴ አምራች በሆኑ አካባቢዎች እያጋጠመ ያለውን ሰፊ የአሲዳማነት ችግርንም ለማቃለል ትኩረት መስጠቱን አስተባባሪው አስታውቀዋል። በዚህ ረገድ ስለ ኖራ አጠቃቀም ለአርሶ አደሩ በሰርቶ ማሳያ በማሳየት በአሲዳማነት የተጠቃ አፈርን በማከም ምርታማነት እንዲሻሻል በፕሮጀክቱ ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የኖራ አቅርቦትን በዘላቂነት ለማረጋገጥ በአማራና በኦሮሚያ ክልሎች ትላልቅ የኖራ ወፍጮዎች እየተተከሉ ሲሆን፣ ለአፈር ለምነት የሚያግዙ ቴክኖሎጂዎችን የማስተዋወቅ ስራም ተያይዞ እየተከናወነ ነው ብለዋል። ለመስኖ ልማት አመቺ በሆኑ አካባቢዎች የ18 የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተፋጠነ እንደሚገኝ የጠቆሙት ኃላፊው፣ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሜካናይዜሽን ማዕከላትን ከመገንባት ጎን ለጎን በአራቱ ክልሎች 49 ትላልቅና መካከለኛ የስንዴ ማከማቻ መጋዘኖችን የመገንባት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። ከአፍሪካ ልማት ባንክ በተገኘ 94 ነጥብ 3 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው ይህ ፕሮጀክት፣ መንግሥት የስንዴን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ለያዘው ስትራቴጂ ስኬታማነት ወሳኝ ድርሻ አለው ብለዋል።    
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የጥራት ደረጃውን የጠበቀ ቡና በብዛት ለማዕከላዊ ገበያ ይቀርባል
Sep 14, 2026 355
ዲላ፣ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በተያዘው በጀት አመት ቡናን በጥራት እና በብዛት አዘጋጅቶ ለማእከላዊ ገበያ ለማቅረብ ከወዲሁ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ቡናና ቅመማ ቅመም ባለሥልጣን ገለጸ። ክልላዊ የቡና ምርት አሰባሰብና ተጓዷኝ ተግባራት ላይ የባለድርሻ አካላት የውይይት መድረክ ዛሬ በዲላ ከተማ ተካሂዷል።   የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አቶ አማኑኤል ብሩ በወቅቱ እንዳሉት በክልሉ የቡና አመራረትና ዝግጅት እየተሻሻለ በመምጣቱ ምርታማነትና ጥራትን ማሳደግ ተችሏል። ከክልሉ በተያዘው 2019 በጀት አመት ቡናን በጥራት በማዘጋጀት በብዛት ለማእከላዊ ገበያ ለማቅረብ በየደረጃው በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በበጀት አመቱ ከ48 ሺህ ቶን በላይ ቡና ለማእከላዊ ገበያ እንደሚቀርብ አመላክተዋል። ጥራት ላለው ቡና የተሻለ ዋጋ መቆረጡ የዘርፉን ተወዳዳሪነት አሳድጓል ያሉት ደግሞ የጌዴኦ ዞን የቡና ላኪዎች ማህበር ሰብሳቢ አቶ ኢያሱ ወራሳ ናቸው።   ባለፈው ዓመት ቡናን በጥራት ከማዘጋጀት ባለፈ በጊዜ ለገበያ እንዲቀርብ መደረጉ ተጠቃሚነታችን እንዲረጋገጥ አስችሏል ብለዋል፡፡ በተያዘው ምርት ዘመንም ጥራት ያለው ቡና ለገበያ ለማቅረብ ከወዲሁ ዝግጅት ማጠናቀቃቸውን አመልክተዋል። ቡና ላኪ አርሶ አደር አሰለፈች ጋን በበኩላቸው የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማነትን ማሳደግ መቻላቸውን ተናግረዋል። በተያዘው ዓመትም ከማሳቸው የሚያገኙትን የቡና ምርት በጥራት በማዘጋጀት በቀጥታ የገበያ ትስስር ለውጭ ገበያ ለማቅረብ እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በመድረኩ አምራቾች፣ ላኪ አርሶ አደሮች፣ አቅራቢ ነጋዴዎችና ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።    
​በዞኖቹ በሰላም እንዲሁም በማህበራዊና ኢኮኖሚ ዘርፎች የተገኙ ውጤቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Sep 14, 2026 281
​ወልድያና ደብረ ማርቆስ ፤ መስከረም 4/ 2019(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በሰሜን ወሎና ምስራቅ ጎጃም ዞኖች በተጠናቀቀው በጀት አመት በሰላም እንዲሁም በማህበራዊና ኢኮኖሚ ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተገኙ አበረታች ውጤቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገለጸ። በሰሜን ወሎና ምስራቅ ጎጃም ዞኖች "አርቆ ማየት፤ አልቆ መስራት" በሚል መሪ ሐሳብ የ2018 በጀት አመት የስራ አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት የዕቅድ ትውውቅ መድረክ ተካሂዷል።   የሰሜን ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አራጌ ይመር በመድረኩ ላይ እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ በሰላም እንዲሁም በማህበራዊና ኢኮኖሚ መስኮች አበረታች ውጤት ተመዝግቧል። በዞኑ የጸጥታ ሃይሉና በህብረተሰቡ የተቀናጀ ጥረት ሰላምን ዘላቂ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል ። በዚህም በመንግስት የቀረበውን የሰላም አማራጭ በመቀበል በርካታ የታጠቁ ኃይሎች መግባታቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል። በስራ እድል ፈጠራ በተከናወኑ ተግባራት ከ180 ሺህ በላይ የሚሆኑ ዜጎች በተለያዩ የገቢ ማስገኛ ዘርፎች መሰማራታቸውን ተናግረዋል። በበጋ መስኖ ልማት ከ231 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ ዘርፉ የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከቱን አንስተዋል ። በዲጂታላይዜሽን ትግበራም አበረታች ውጤት መመዝገቡን ጠቁመው በተያዘው 2019 በጀት አመት በየዘርፉ የተመዘገቡ ውጤቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል በትኩረት እንደሚሰራ አስታውቀዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የሰሜን ወሎ ዞን ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ወንድሙ በበኩላቸው የአመራሩን የማስፈጸም አቅም በመገንባት በልማትና መልካም አስተዳደር ስራዎች ላይ ለውጥ እንዲመጣ ተደርጓል ብለዋል። በዞኑ ከጉባላፍቶና ግዳን ወረዳዎች ነዋሪዎች መካከል አቶ ያለው ገደፋውና ወይዘሮ ደብረወርቅ ማዕረግ፤ እንደገለጹት መድረኩ በተጠናቀቀው በጀት አመት የታዩ ክፍተቶችን በማረም በተያዘው የበጀት ዓመት የተሻለ ለመፈጸም የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል። በተያያዘ ዜና የምስራቅ ጎጃም ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኑርልኝ ብርሃኑ እንደገለጹት በ2018 በጀት ዓመት ዞኑ በልማትና መልካም አስተዳደር ስኬቶች የተመዘገቡበት ነው ።   በበጀት ዓመቱ በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በኢንቨስትመንትና ሌሎች ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የላቀ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን አስረድተዋል። ዞኑ በበጀት አመቱ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎች በክልሉ ከሚገኙ ዞኖች ሶስተኛ ደረጃ ይዞ ማጠናቀቁ የዚሁ ማሳያ ነው ሲሉ አብራርተዋል። በተያዘው በጀት አመት በሁሉም ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አመላክተዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የምስራቅ ጎጃም ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ተስፋዬ በላይ በበኩላቸው በፓርቲው አመራር ሰጪነት በተከናወኑ የሰላምና የልማት ስራዎች ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል። በዞኖቹ በተካሄደው መድረክ ከዞን፣ ወረዳና የከተማ አስተዳደሮች የተወጣጡ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች እንዲሁም የህብረተሰብ ተወካዮች ተሳትፈዋል ።
የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም አጎልብቷል
Sep 14, 2026 374
አዲስ አበባ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር ዕድገትን በማፋጠን ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም ማጎልበቱን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶች ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር አዝጋሚና መዋቅራዊ የዕድገት ስብራትን በማከም፣ ዓለም አቀፍ ንግድና ኢንቨስትመንትን በማበራታታት በሁሉም ዘርፍ ዕድገትን እያሳለጠ ነው። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶች ለኢዜአ እንዳሉትም፤ የኢትየጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የብዝኅ ኢኮኖሚ ልማት ፍኖትን በማብሰር ዕድገት የሚያፋጥን እመርታዊ ውጤት እያስገኘ ነው። የኢኮኖሚ ዘርፎች እመርታዊ ውጤትም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ኢትዮጵያን ወደተሻለ የብልፅግና ምዕራፍ ማሸጋገር ያስቻሉ ጠንካራ መሰረቶችን እንደጣሉ ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አስራት አፀደወይን (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ግዙፍ ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም በማጎልበት አመርቂ ውጤት አስገኝቷል ብለዋል። የመደመር መንግሥት ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት የመፈጸም አቅም የትውልድን መሻት በመቅረጽ አኩሪ የአስተሳስብ ለውጥ የመጣባቸው መሆኑን አንስተዋል። ለአብነትም የመገጭ የመስኖና ንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክትን ጨምሮ ለበርካታ ዓመታት የሕዝብ የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ሆነው የቆዩ ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት የሚገነቡበትን ዕድል እንደፈጠረ ገልጸዋል። መንግሥት ለሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ የሰጠው ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥርም የከተማና ገጠር የልማት ውጤታማነትን በማሻሻል ኢትዮጵያን ተምሳሌት ሀገር እያደረጋት መሆኑን ተናግረዋል። የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ደረጄ እንግዳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የፖሊሲ እርምጃ ቀጣይነት ያለው ዕድገት እያስመዘገበ ነው ብለዋል።   የመደመር መንግሥት ዕድግትን በማፋጠን የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የሚታዩና የሚጨበጡ ውጤቶችን ማስገኘት እንደቻለ ጠቅሰዋል። የፖሊሲ እርምጃውም ኢትዮጵያ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር ታላቁ የሕዳሴ ግድብን ጨምሮ በከተማና ገጠር ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መፈጸም እንዳስቻላት አስረድተዋል። በተጨማሪም የጉባ ብስራት የሆኑትን እንደ ቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያና ሌሎች ግዙፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ አበርክቶ ያላቸው ዐበይት ፕሮጀክቶችን ማስጀመር እንዳስቻላት አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የተሰናሰለ የከተማና ገጠር ሁለንተናዊ የልማት ጉዞም አፍሪካዊት የብልፅግና ተምሳሌት ኢትዮጵያን ለቀጣዩ ትውልድ የሚያሻግር ታሪክ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።     በኢትዮጵያ በከተማና ገጠር በጥራትና ፍጥነት ተገንብተው የሚጠናቀቁ የልማት ፕሮጀክቶች የመንግሥትን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጡ ናቸው ያሉት ደግሞ የሰላሌ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፈየራ ዲንሳ (ዶ/ር) ናቸው። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የፖሊሲ እርምጃም ድኅነትና ኋላቀርነትን የሚገቱ የልማት ተነሳሽነቶችን በማስተግበር ሀገርን ወደ ተሻለ የዕድገት ምዕራፍ እያስፈነጠረ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ከነበረበት አደጋ ተላቆ ለምርቃት መብቃት በራስ መተማመን መንፈስን በማጎንጸፍ ተጨማሪ ግዙፍ ፕሮጀክቶች እንዲጀመሩ ማስቻሉን ተናግረዋል።   የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዑባህ አደም (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የልማት ስኬቶች የዜጎችን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ዕድገትን የሚያፋጥን አቅም መፍጠራቸውን ገልጸዋል። ለአብነትም የኢትዮጵያ ከተማና ገጠር የኮሪደር ልማት ውጤቶች የሀገርን ገጽታ በመገንባት አቅዶ የመፈጸም አቅምን ያጎለበቱ ውጤታማ የልማት ሥራዎች መሆናቸውን አንስተዋል። በቀጣይም ሀገር በቀል የፖሊሲ እርምጃዎች የፈጠሩትን ዕድል በመጠቀም መንግሥትና ሕዝብ የሀገርን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት ለማረጋገጠ በርብርብ መስራት እንደሚጠበቅ አስገንዝበዋል።
የህዝብን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት አጠናክሮ ለማስቀጠል ርብርብ ይደረጋል -አስተዳደሩ
Sep 14, 2026 129
መተማና ሰቆጣ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- የህዝብን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን በላቀ ቅንጅትና ትብብር ለማስቀጠል ርብርብ እንደሚደረግ ተጠቆመ። በምዕራብ ጎንደር ዞን እና በዋግ ህምራ ብሄረሰብ አስተዳደር የ2018 የበጀት ዓመት እቅድ አፈፃፀም እና የ2019 ዓ.ም እቅድ ትውውቅ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   የምዕራብ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ በገንዳ ውሃ ከተማ እየተካሄደ ባለው መድረክ እንዳሉት፤ ባለፈው የበጀት ዓመት በተደረጉ የተቀናጁ ጥረቶች አስተማማኝ ሰላም በመገንባት አበረታች ውጤት ተመዝግቧል። ለአካባቢው ሰላምና መረጋጋት መስፈን የህዝቡ ንቁ ተሳትፎና ያልተቋረጠ ድጋፍ ቁልፍ ሚና መጫወቱን ገልፀዋል። በበጀት ዓመቱ በግብርና ልማት፣ በገቢ አሰባሰብ፣ በከተማ ልማትና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተሻሉ አፈጻጸሞች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፤ የተገኙ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል በተሻለ መልኩ ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። የዞኑ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ እንዳለው ማሩ በበኩላቸው፤ ህዝቡ ከመንግስት ጎን በመቆም ላሳየው አበረታች የልማትና የሰላም ፍላጎት ምስጋና አቅርበዋል።   በ2019 የበጀት ዓመት የታቀዱ የልማትና የመልካም አስተዳደር ግቦችን ለማሳካት የፓርቲው አመራርና አባላት ህዝቡን በንቅናቄ በማሳተፍ በቁርጠኝነት እንደሚሰሩም ነው የተናገሩት። በተመሳሳይ በዋግ-ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር በ2019 በጀት ዓመት የአካባቢን ፀጋ መሰረት ያደረጉ እቅዶችን አቅምን አሟጦ ለመስራት ዝግጅት መደረጉን የገለፁት ደግሞ የሰቆጣ ከተማ ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዳግም ባይነሳኝ ናቸው።   በተጠናቀቀው ዓመት ውስብስብ ችግሮችን በመቋቋም በርካታ የልማት ስኬቶችን ማስመዝገብ መቻሉን አስታውሰው፤ በአዲሱ በጀት ዓመት የተመዘገቡ ስኬቶችን በላቀ ደረጃ ለመፈፀም የሚያስችል አሰራር መዘርጋቱን ተናግረዋል። የአመራሩን ቅንጅታዊ አሰራር ይበልጥ በማሳደግ ህዝብን ያሳተፉ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራትን ማስፋፋት የአዲሱ በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ገልፀዋል። በየደረጃው የሚገኙ አስፈፃሚዎችም ተጨባጭና ውጤታማ እቅድ በማቀድና በመፈፀም ለስኬቱ ሊረባረቡ እንደሚገባ አሳስበዋል። ለተከታታይ ሶስት ቀናት በሚካሄዱት መድረኮች የወረዳና ከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች ተሳታፊ ሆነዋል።  
በባህር ዳር ከተማ አስተማማኝ ሰላምና ተጨባጭ የልማት ስራዎችን ማከናወን ተችሏል
Sep 14, 2026 94
ባህር ዳር፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦ በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው አስታወቁ። «አርቆ ማየት፤ አልቆ መሥራት» በሚል መሪ ሐሳብ የመንግሥትና ፓርቲ የ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት የዕቅድ ትውውቅ መድረክ መካሄድ ጀምሯል።   ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው በዚሁ መድረክ እንደገለጹት፤ በከተማዋ የፀጥታ አካላትና በሕዝቡ ጠንካራ ቅንጅት አስተማማኝ ሰላምን ማስፈን ተችሏል። ባህር ዳርን ውብ፣ ጽዱ እና አረንጓዴ የማድረግ ተግባር በተጨባጭ እውን ማድረግ መቻሉንና የመሠረተ ልማት ግንባታዎች የከተማዋን ገጽታ በከፍተኛ ደረጃ መቀየራቸውን ገልጸዋል። የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶችም አዲስ የሥራ ባህል ተፈጥሮባቸው በአጭር ጊዜና በጥራት ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ መደረጉንም አንስተዋል። በከተማዋ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ቀልጣፋ እና ፍትሐዊ አገልግሎት በመስጠት ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ የተቻለ ሲሆን ከ75 ሺህ በላይ ነዋሪዎች አገልግሎቱን እንዲያገኙ መደረጉን ጠቁመዋል።   የከተማ አስተዳደሩ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞላ ሁሴን በበኩላቸው፤ በከተማዋ ከጊዜ ወደ ጊዜ አስተማማኝ ሰላም እየሰፈነ መምጣቱን ገልጸዋል። የተገኘው ሰላም ለማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማቶች መሳካት ቁልፍ መሠረት በመሆኑ ቀጣይነት እንዲኖረው ሁለንተናዊ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የታዩ ክፍተቶችን በማረም በአዲሱ በጀት ዓመት የላቀ ውጤት ለማስመዝገብና ከተማዋን ይበልጥ ለማልማት ሁሉም በቅንጅት መስራት እንዳለበት አሳስበዋል።
በዞኑ በምርት ዘመኑ 28 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ የሚያስችሉ ተግባራት እየተካሄዱ ነው
Sep 14, 2026 109
ባህር ዳር፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ጎንደር ዞን በመኸር ወቅት ከለማው 641 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ከ28 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ የሚያስችል የተባይ አሰሳና የአረም መከላከል ስራ እየተከናወነ ይገኛል።   የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ የሺጥላ ፈቃዴ እንደገለጹት፤ በዞኑ በኩታ ገጠም አሰራር እየለሙ ያሉትን እንደ ሩዝ፣ ጤፍ፣ ስንዴ እና ገብስ ያሉ ሰብሎችን ከአረምና ተባይ ነፃ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ ነው። ሙሉ የግብርና ፓኬጅ፣ የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችና የአፈር ለምነት ማሻሻያዎች በጥቅም ላይ በመዋላቸው ሰብሉ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝና የታቀደው ምርት እንደሚገኝ ተናግረዋል።   የዞኑ አርሶ አደሮች በበኩላቸው፤ በባለሙያዎች ምክረ-ሃሳብ ታግዘው ማሳቸውን በየዕለቱ በመቃኘትና በማረም ላይ እንደሚገኙ ገልጸው፣ የኩታ ገጠም አሰራርና ዘመናዊ ግብዓቶችን መጠቀም ከቤተሰብ ፍጆታ የተረፈ ምርት ለገበያ ለማቅረብ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል።  
በዞኑ በማር ምርት የተገኘው ውጤት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Sep 14, 2026 178
ዲላ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በማር ምርት የተገኘውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያስችሉ ተግባራትን መጀመራቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በዞኑ እየተከናወነ ያለውን የጥምር የግብርና ስርዓት ለንብ ማነብ ስራ አመቺ ሁኔታ በመፍጠሩ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን ተችሏል። በጥምር ግብርናው ቡና፣ ፍራፍሬ፣ ሃገር በቀል ዛፎችንና የተለያዩ እጽዋቶችን ከማልማት ባለፈ ለንብ ማነብ ስራዎችም የተመቸ ምህዳር ፈጥሯል ነው የሚሉት። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ በዞኑ ከተከናወነው የንብ ሃብት ልማት ስራ ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱ ተገልጿል። በዚሁ ወቅት በተለይ ተራሮችን የማር ምርት ማዕከል ለማድረግ በተደረገው ጥረት በዲላ ዙሪያ፣ ወናጎ፣ ይርጋጨፌና ኮቾሬ ወረዳዎች በተመረጡ ቦታዎች ከአንድ ሺህ በላይ ዘመናዊ ቀፎ ማስቀመጥ መቻሉን ተናግረዋል። በንብ ማነብ ስራ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች በተጨማሪ በማህበር የተደራጁ ወጣችን ወደ ስራው እንዲገቡ ማድረግ በመቻሉ በዘርፉ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን እንደተቻለም ነው የገለጹት። በአዲሱ በጀት ዓመትም የአካባቢውን የደንና የእጽዋት ሽፋን በመንከባከብ ንብ በማነብ ከማር ምርት የሚገኝ ገቢን ከፍ ለማድረግ ወደ ስራ መገባቱን ነው ያመለከቱት። በወረዳው በራኮ ቀበሌ በግኖ ተራራ ላይ ከ200 በላይ ዘመናዊ ቀፎዎች በማስቀመጥ የንብ ማነብ ስራ እየተካሄደ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የኮቾሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ዳዊቶ ጀቦ (ዶ/ር) ናቸው። ይህም የማር ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፍ የተፈጥሮ ጸጋዎችን በመንከባከብና በማልማት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ጥራት ያለው የተፈጥሮ ማር በማምረት ለአካባቢው አርሶ አደሮች፣ ወጣቶች እና ሴቶች ተጨማሪ የገቢ ምንጭ መፍጠር እንደተቻለም ነው ያነሱት። በማር ምርት ስራ ላይ የተሰማሩት አርሶ አደር ብዙነሽ ሐልቹ፤ ከ70 በላይ በሆኑ ባህላዊና ዘመናዊ ቀፎዎቻቸው በአመት ሁለት ጊዜ የማር ምርት እንደሚያገኙ ነው የተናገሩት። የማር ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆኑንም ነው የተናገሩት። ከዘመናዊ ቀፎ የሚገኝ የማር ምርት የተሻለ ጥራትና ብዛት ያለው መሆኑን ያነሳው ደግሞ በማር ምርት ስራ ላይ የተሰማራው ወጣት ማርቆስ ጌታሁን ነው። በወረዳው ያለው የተፈጥሮ ሃብት ለንብ ማነብ ስራ ምቹ በመሆኑም ጥራት ያለው ማር በማምረት በስፋት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆኑን ነው የተናገረው።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኃይል አቅርቦቱን በእጥፍ በማሳደግ የቀጣናውን የኢኮኖሚና የኃይል ትስስር እያጠናከረ ነው
Sep 14, 2026 602
አዲስ አበባ፤መስከረም4 /2019 (ኢዜአ):-ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሀገሪቱን የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ከእጥፍ በላይ ከማሳደግ ባለፈ የቀጣናውን የኃይል ትስስር እያጠናከረ እንደሚገኝ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር አሸብር ባልቻ አስታወቁ። ዋና ሥራ አስፈጻሚው ለኢዜአ እንዳሉት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያውያን ጽናት፣ አንድነትና ቁርጠኝነት በተግባር የተገለጠበት «ዳግማዊ ዓድዋ» መሆኑን ተናግረዋል። የግድቡ ግንባታ ኢትዮጵያ በራሷ አቅም የላቀ ስኬት ማስመዝገብ እንደምትችል ለዓለም ያስመሰከረችበት፤ ብሎም አዲስ የታሪክ ምዕራፍ የከፈተ ታላቅ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። ግድቡ ተመርቆ ወደ ሙሉ ሥራ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ የሀገሪቱን የኃይል ማመንጨት አቅም በእጥፍ ከመጨመሩም በላይ፣ ኢትዮጵያ ከዘርፉ የምታገኘውን የውጭ ምንዛሬ ገቢ በእጅጉ ማሳደጉን ገልጸዋል። ተቋሙ በ2018 በጀት ዓመት በሀገር ውስጥ ካገኘው ከፍተኛ ገቢ በተጨማሪ ከግማሽ ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማግኘቱን ጠቁመው፤ ለዚህ ታሪካዊ ስኬት የታላቁ ህዳሴ ግድብ ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን አስረድተዋል።   በዚህም የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ ከዕዳ ተላቆ ወደ ትርፋማነት እንዲሸጋገር ማስቻሉን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በተመጣጣኝ ዋጋ ለጎረቤት ሀገራት ኃይል እያቀረበች መሆኑን የጠቆሙት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ የግድቡ ወደ ሥራ መግባት ለቀጣናዊ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ ትስስር ማደግ አይነተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ለኬንያ፣ ለጅቡቲ፣ ለሱዳን እና በከፊል ለታንዛኒያ የኤሌክትሪክ ኃይል በማቅረብ ላይ መሆኗን የጠቆሙት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ ወደ እነዚህ ሀገራት ከሚላከው አጠቃላይ ኃይል ውስጥ 52 በመቶ የሚሆነው ድርሻ ከህዳሴው ግድብ የሚመነጭ መሆኑን አመላክተዋል።   የኃይል አቅርቦቱን በእጥፍ በማሳደግ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ብቻ ሳይሆን ለጎረቤት ሀገራትም ከፍተኛ የኤሌክትሪክ አቅርቦት ጥቅም እየሰጠ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።  
በጅማ ዞን የተቀናጀ የቡና ልማትና የጥራት እንክብካቤ ስራን በስፋት በመተግበር አርሶ አደሮች ተጠቃሚ ሆነዋል
Sep 14, 2026 331
ጅማ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን የተቀናጀ የቡና ልማትና የጥራት እንክብካቤ ስራን በስፋት በመተግበር ከምርቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ገለጹ። በጅማ ዞን ቀደም ሲል የሚሰበሰበው የቡና ምርት በጥራትና በድህረ-ምርት አያያዝ ጉድለት ምክንያት አርሶ አደሩን በሚፈለገው ልክ ተጠቃሚ ሳያደርግ ቆይቷል። ይህንን ችግር ለመቅረፍ በዞኑ አመራርና ባለሙያዎች አስተባባሪነት ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተቀናጀ የቡና ልማትና የጥራት ማሻሻያ ተዘጋጅቶ ወደ ተግባር ተገብቷል። በልማቱ ተሳታፊና ተጠቃሚ የሆኑት አርሶ አደሮች እንዳሉት፣ ጥራቱን የጠበቀ የቡና ምርት በቀጥታ ለገበያ የሚያቀርቡበት አሰራር በመዘርጋቱ፣ ከቀጥታ የገበያ ትስስሩ የሚገኘው ገቢ ተጠቃሚነታቸውንና የኑሮ ደረጃቸውን እንዲሻሻል አድርጎታል።   በዞኑ የጎማ ወረዳ አርሶ አደር ሙስጠፋ አባ ቀኖ፣ በአሁኑ ወቅት መንግስት ባመቻቸው የቀጥታ የገበያ እድል የደላሎች ጣልቃ ገብነት በመቅረቱ፣ ቡናቸውን በጥራትና በስፋት አዘጋጅተው ለገበያ ማቅረብ መቻላቸውን ተናግረዋል። ቡናን በቀጥታ ለውጭ ገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን ጠቅሰው፣በጥራት እና በቴክኖሎጂ በተደገፈው አሰራር ከአንድ ሄክታር እስከ 10 ኩንታል ምርት በማግኘት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። አሰራሩ ገቢያቸውን ከማሳደጉም በላይ ለሀገሪቱ የውጭ ምንዛሬ ግኝት የድርሻቸውን እንዲያበረክቱ ማስቻሉንም አብራርተዋል።   ሌላኛው የዞኑ አርሶ አደር ዛኪር አባፊጣ በበኩላቸው፣ ባለፉት ዓመታት ከተለምዷዊ አሰራር በመላቀቅ ቡናን በኩታገጠም በጥራት ማምረት መጀመራቸውን ገልጸዋል። በኩታገጠም የሚከናወነው የልማት ስራ የሙያና የቴክኖሎጂ ድጋፍን በጥንቃቄ ለመተግበር በመርዳቱ፣ የምርት ጥራትንና ምርታማነትን በከፍተኛ ደረጃ እንዳሳደገው ገልጸዋል። በቡና ልማት ትርፋማ መሆናቸውን የገለጹት አርሶ አደር ዛኪር፣ ከዘርፉ ባገኙት ገቢ በቅርቡ ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ጠቅሰዋል። ይህም በጥራትና በኩታገጠም የተመራ የግብርና ልማት አርሶ አደሩን ወደ ባለሃብትነት ለማሸጋገር ያለውን አቅም ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።   ወጣት አርሶ አደር ቡሊ አባመጫ በበኩሉ፣ ቡናን በጥራት በማምረት ለገበያ እያቀረበ መሆኑን ገልጿል። በቅርቡ በተጠናቀቀው የቡና ምርት ዘመን ከ20 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ ጥራት ያለው ቡና ለገበያ ማቅረቡንና ከዘርፉ የሚገኘው ጥቅም የወጣቶችን የኢኮኖሚ ተሳትፎ የሚያጎለብት መሆኑን አብራርቷል። አርሶ አደር ኤሊያስ አባሰዲም፣ ከዚህ በፊት ከሚያመርቷቸው የቡና ተክሎች በተጨማሪ በየወቅቱ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ምርጥ ዘር የቡና ችግኞች ፍሬ አፍርተው ምርት መስጠት መጀመራቸውን ተናግረዋል።   አሰራሩ የቀደመውን የምርት አቅም በማጎልበት ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ገልጸው፤ ይህም የምርት መጠናቸውንና አምራችነታቸውን በከፍተኛ ሁኔታ ከፍ እንዳደረገላቸው ገልጸዋል። አርሶ አደሮቹ እንደገለጹትም፣ መንግስት ለቡና ምርት ጥራትና መስፋፋት በሰጠው ትኩረት አማካኝነት አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍና ክትትል መደረጉ ለቡና ልማቱ መስፋፋትና ለውጤታማነቱ ዋና ምክንያት ነው።   የጅማ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም እንደገለጹት፣ በዞኑ ባለፉት ሰባት ዓመታት የቡና ምርት ሽፋን ከ330 ሺህ ሄክታር ወደ 700 ሺህ ሄክታር አድጓል። የቡና ልማት ሽፋኑ በከፍተኛ ደረጃ ማደጉ ምርታማነትንና የጥራት ደረጃን ከመጨመሩ ባሻገር የአርሶ አደሩን የገቢ አቅም ያጎለበተ መሆኑንም አብራርተዋል። አርሶ አደሩ ምርቱን በቴክኖሎጂና በኩታገጠም በጥራት በማልማት ያለምንም ጣልቃ ገብነት በቀጥታ ለገበያ የሚያቀርብበት ምቹ ሁኔታም ተፈጥሯል ብለዋል። በዚህም በተጠናቀቀው ዓመት ከተሰበሰበው 341 ሺህ ቶን ቡና ውስጥ 94 ሺህ ቶኑ ለዓለም አቀፍ ገበያ የቀረበ ሲሆን፣ ይህም ለሀገር የውጭ ምንዛሬ ከማስገኘት ባሻገር አርሶ አደሩን የኢንቨስትመንት ባለቤት እስከ መሆን ያደረሰ አቅም ፈጥሯል ብለዋል።    
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አባልና አጋር ሀገራትን ባሳተፈው የብሪክስ ፕላስ የምክክር መድረክ ላይ፤ጠንካራ የአፍሪካ ውክልና እንዲኖር ጥሪ አቅርበዋል
Sep 13, 2026 619
አዲስ አበባ፤መስከረም 3 /2019 (ኢዜአ):-አባልና አጋር ሀገራትን ባሳተፈው የብሪክስ ፕላስ የምክክር መድረክ ላይ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጠንካራ የአፍሪካ ውክልና እንዲኖር፣ የፋይናንስ እና የገበያ ተደራሽነት ይበልጥ እንዲሰፋ እንዲሁም ንግድ፣ ኢንቨስትመንት እና ትስስርን ለማሳደግ ተግባራዊ እርምጃዎች እንዲወሰዱ ጥሪ አቅርበዋል። ‎‎በዚህ አውድም፣ የኒው ዴቨሎፕመንት ባንክ አድማሱን በመላው አፍሪካ እንዲያስፋፋ የባንኩን ቢሮ በአዲስ አበባ ለማስተናገድ ኢትዮጵያ በሙሉ አቅም ዝግጁ መሆኗን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። ‎‎በተጨማሪም በአዲስ አበባ የሚካሄደው ኮፕ 32 በብሪክስ ሙሉ ድጋፍ ለአየር ንብረት ጥበቃ ሥራዎች እና ለዘላቂ ልማት መፋጠን ሁሉንም ድምፆች የሚያሰባስብ ሁሉን አቀፍ መድረክ ሆኖ ማገልገል እንደሚችል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል። ‎‎#PMOEthiopia
የኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ድምጾች በብሪክስ መድረክ ተስተጋብተዋል-የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
Sep 13, 2026 395
አዲስ አበባ፣መስከረም 3/ 2019 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ድምጾች በብሪክስ መድረክ መስተጋባታቸውን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለፀ፡፡ አገልግሎቱ በዛሬው ዕለት ባወጣው መግለጫ፤ የኢትዮጵያ በሳል ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ብዙ ሀገራት የሚመኙትን የብሪክስ አባል የመሆን መሻት እንድታሳካና ተጠቃሚ እንድትሆን አስችሏታል ብሏል። የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡ የኢትዮጵያ ስትራቴጂያዊ ድምጾች በብሪክስ መድረክ ተስተጋብተዋል! ብሪክስ ወደ ሰፊ ጥምረት አድጓል፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ አሁን 11 ሙሉ አባላት ያሉት ሲሆን በሩሲያ ካዛን ጉባኤ ይፋ የተደረጉ 10 አጋር አገራትንም በልዩ የአጋርነት ማዕቀፍ በማካተት ተጽእኖውን አጠናክሯል። የብሪክስ ጥምረት የዓለምን ሕዝብ ቁጥር ግማሽ ያህል፣ የዓለም አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርትን (GDP) 40 በመቶ ገደማ፣ እና የዓለምን ንግድ ሩብ ያህል ይወክላል። መጠኑ እጅግ ግዙፍ ነው። ብሪክስ ከእንግዲህ ተራ ጥምረት ብቻ አይደለም፤ በዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ሥርዓት ውስጥ ዋነኛ ኃይል እየሆነ ነው።   የብሪክስ አባል ሀገራት በአለምአቀፍ ደረጃ የተጽዕኖ አድማሳቸው የሰፋ፣ የዓለም አቀፍ የሀብት፣ የቴክኖሎጂ እና የሰፊ ገበያ ማዕከል መዳረሻ ናቸው። የኢትዮጵያ በሳል ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ብዙ ሀገራት የሚመኙትን የዚህ ጥምረት አባል የመሆን መሻት እንድታሳካና ተጠቃሚ እንድትሆን አድርጓታል። በዚህ ሂደት ኢትዮጵያ የራሷን ጥቅም ከማስጠበቅ ባለፈ ለአፍሪካ ድምፅ በመሆን የአህጉሪቱን ጥያቄዎች እና የጋራ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሥራዎችን በቁርጠኝነት እየሠራች ትገኛለች። ከቀሪ የቤት ሥራዎች አንዱ ይህን ታሪካዊ ዕድል በመጠቀም የጥምረቱን ግዙፍ አቅሞች በማስተሳሰር የላቀ እሴት መፍጠር እና ይህ እሴት ሀብቱ በቀጥታ በሚገኝበት አካባቢ እንዲመረት ማድረግ ነው። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ በማዕድን ልማት፣ በታዳሽ ኃይል እና በማደግ ላይ ባለው የኢንዱስትሪ መሠረቷ ላይ እነዚህን ስትራቴጂካዊ አጋርነቶች እውን ለማድረግ ሙሉ ዝግጁነት አላት።   በማዕድን ዘርፍ ኢትዮጵያ ያሏትን እንደ ሊቲየም፣ ታንታለም እና ፖታሽ ያሉ ለዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ እና የኢነርጂ ሽግግር ወሳኝ የሆኑ ሀብቶችን በሀገር ውስጥ በማቀነባበር የኢንዱስትሪ እሴት ሰንሰለቱን ለመቀላቀል ሰፊ ሥራዎችን እየሠራች ይገኛል። ይህ እንቅስቃሴ የሀብት ባለቤት የሆኑ ሀገራት ከጥሬ ዕቃ ላኪነት ወጥተው የተጠናቀቁ ምርቶች አምራች እንዲሆኑ የሚያስችል የጋራ የኢኮኖሚ ምዕራፍ ይፈጥራል። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ያላትን ግዙፍ የታዳሽ ኃይል አቅም በመጠቀም አረንጓዴ እና ንጹህ የኢነርጂ አቅርቦትን ለሀገራት ማዳረስ ትችላለች። የውኃ፣ የጂኦተርማል እና የሶላር ኃይል ሀብቶችን በማልማት ለቀጣናው እና ለአጋሮች አስተማማኝ የኃይል ማዕከል ለመሆን የሚያስችል ጠንካራ መሠረት ይጥላል። ኢኮኖሚያዊ ትስስሩ ከሀብት ማውጣትና ማቀነባበር ባሻገር በቴክኖሎጂ ሽግግር እና በተቋማዊ ጽናት ላይ የተመሠረተ መሆን ይኖርበታል። የአሠራር ሥርዓቶቻችንን በማጠናከር እና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (AI)ን ጨምሮ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች የአፍሪካን ልማታዊ እና ማህበራዊ ፍላጎቶች በትክክል እንዲያገለግሉ የጋራ ጥረቶችን ማቀናጀት ያስፈልጋል። ለዚህም ኢትዮጵያ ቁርጠኛ ናት። ለዘላቂ ዕድገት መረጋገጥ የፋይናንስ ሥርዓቶች ፍትሃዊ መሆን አለባቸው፤ በዚህ ረገድ በማደግ ላይ ያሉ ሀገራትን የዕዳ ጫና የሚያቃልል አስተማማኝ እና ፍትሃዊ የዕዳ እፎይታ ሒደት ማሳደግ ወሳኝ ነው። የብሪክስ መድረክ የደቡብ-ደቡብ ትብብርን በመጠቀም ፍትሃዊ የዓለም አቀፍ የፋይናንስ ሥርዓት እንዲዘረጋ ጠንካራ ድምፅ ማሰማት የሚችልበት አቅም አለው። ከኢኮኖሚ ሽግግር ጎን ለጎን የአየር ንብረት ጥበቃ ሥራዎችን ከምግብ ዋስትና እና ከዘላቂ ልማት ጋር ማስተሳሰር ይገባል። እንደ ኢትዮጵያ «የአረንጓዴ አሻራ» ተነሳሽነት ያሉ አሠራሮች ለአየር ንብረት ጽናት የሚሰጡትን አስተዋጽኦ በማስፋት የብሪክስ መድረክ የጋራ ትብብርን ወደ ተጨባጭ እሴት፣ ጽናት እና ዘላቂ የጋራ ዕድገት ለመለወጥ የሚያስችል ታሪካዊ ዕድል ይፈጥራል። ኢትዮጵያም ይህን ዕድል የአፍሪካ ድምጽ በመሆን ጭምር መጠቀም ጀምራለች ።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም