ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኮሪደር ልማትና የፅዱ ኢትዮጵያ ኢኒሼቲቭ የደብረ ብርሃን ከተማን ለኢንቨስትመንትና ቱሪዝም ተመራጭ እያደረጓት ነው
Aug 17, 2026 132
ደብረ ብርሃን፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፡-የኮሪደር ልማትና የፅዱ ኢትዮጵያ ኢንሼቲቭ የደብረ ብርሃን ከተማን ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ተመራጭ እያደረጓት መሆኑን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። በከተማ አስተዳደሩ የምግብ ዋስትናና ሴፍቲኔት፣ የአካባቢ ጥበቃ እንዲሁም የጽዳትና ውበት ተጠሪ ጽሕፈት ቤቶች “ፅዱ ኢትዮጵያ ለትውልድ” በሚል መሪ ሐሳብ የጋራ የንቅናቄ መድረክ አካሂደዋል። በመድረኩም የከተማዋ ነዋሪዎች፤ የኮሪደር ልማትና የፅዱ ኢትዮጵያ ኢንሼቲቭ የደብረ ብርሃን ከተማን ለኢንቨስትመንትና ቱሪዝም ተመራጭ እያደረጓት ነው ብለዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ደስታ ፀጋ፤ በከተማው የተተገበረው የኮሪደር ልማት ከተማዋን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ አድርጓታል ብለዋል። ነዋሪዎችም የአካባቢያቸውን ጽዳትና ንጽህና በመጠበቅ የከተማዋን እድገት ለማፋጠን የበኩላቸውን ድርሻ እየተወጡ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ሌላኛዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ ገነት ሀይለሚካኤል በበኩላቸው፤ አስተዳደሩ የከተማዋን ሰላም ከማረጋገጥ ጎን ለጎን ዘላቂ እድገትን የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎችን እየከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በከተማው እየተሰራ ያለው የኮሪደር ልማትና የፅዱ ኢትዮጵያ ኢኒሼቲቭ ተግባራት ለዚህ ማሳያ መሆናቸውን አስረድተዋል። የከተማዋን ገጽታ ይበልጥ ለማድመቅም ከራስ ግቢ እስከ ዋናው መንገድ ያለውን በማህበረሰብ ተሳትፎ በማፅዳት የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ተናግረዋል። በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ አማካሪ አቶ ታጠቅ ገድለአማኑኤል እንዳሉት፤ የተከናወኑ የልማት ስራዎች ከተማዋን በኢንዱስትሪ፣ በኢንቨስትመንትና በቱሪዝም ተመራጭ እንድትሆን አድርገዋታል። በፅዱ ኢትዮጵያ ኢንሼቲቭ ሁሉም ነዋሪዎች ከመኖሪያ ቀያቸው እስከ መንደራቸው ያሉ አካባቢዎችን ጽዱና የተዋቡ በማድረግ ጤናማና አምራች ዜጋ ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት እያገዙ መሆኑን አስረድተዋል። በቀጣይም የኮሪደር ልማቱን ወደ ገጠር በማስፋት በከተማው እየመጣ ካለው ለውጥ ጋር በማስተሳሰር ፈጣን እድገት ለማስመዝገብ በትኩረት እንደሚሰራም ተናግረዋል።   የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር የምግብ ዋስትናና ሴፍትኔት ተጠሪ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ግርማ ዲባቤ በበኩላቸው፤ በከተማ ሴፍትኔት ፕሮግራም የሚከናወኑ የልማት ስራዎች የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ለመፍታት አስችለዋል ብለዋል። በቀጣይም የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት በሚያሳድጉ የስራ ዘርፎች ላይ በማተኮር የተጀመረው ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።  
መንግስት ከዋናው የኤሌክትሪክ ሃይል መስመር ውጪ ባሉ አካባቢዎች የፀሐይ ኃይል ልማት ፕሮጀክቶችን በስፋት እየተገበረ ነው -የውሃና ኢነርጂ ሚንስቴር
Aug 17, 2026 97
ጭሮ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ) ፡-መንግስት ከዋናው የኤሌክትሪክ ሃይል መስመር ውጪ ባሉ አካባቢዎች የፀሐይ ኃይል ማመንጫዎችን ለማስፋፋት የሚያደርገው ጥረት የኤሌክትሪክ ተደራሽነትን እያሳደገ መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ገለጸ። በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ሐዊ ጉዲና ወረዳ ከ800 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባው የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ተገለጸ።   የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) ፕሮጀክቱን መርቀው ስራ ባስጀመሩበት ወቅት፤ ከዋናው መስመር ውጪ የሚከናወኑ የኃይል ማዳረስ ሥራዎች የኤሌክትሪክ ተደራሽነትን እያሳደጉት መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የአገሪቱ የኤሌክትሪክ ሽፋን ከአምስት ዓመት በፊት ከነበረበት 43 በመቶ ወደ 63 በመቶ ማደጉን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፣ ለዚህ እድገት የፀሐይ ኃይል ማመንጫዎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ተናግረዋል።   በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ሐዊ ጉዲና ወረዳ ተገንብተው ዛሬ የተመረቁት የሃሎ ጉባ፣ ቶርባን፣ ባቴ እና ሃሮ ኤባ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ጣቢያዎች ከ5 ሺህ በላይ ቤተሰቦችን የማገልገል አቅም ያላቸው ናቸው ብለዋል። በገጠር አካባቢዎች የኤሌክትሪክ አገልግሎትን የማዳረስ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፣ኅብረተሰቡም የተገነቡትን ፕሮጀክቶች የመጠበቅና የመንከባከብ ሀላፊነቱን እንዲወጣ አስገንዝበዋል። የምዕራብ ሐረርጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ተሾመ ከበደ በበኩላቸው፣ በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከስድስት ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት የበቁ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በቅርቡ በዞኑ የአርብቶ አደር ወረዳ ሆና በተቋቋመችው ሐዊ ጉዲና ወረዳ የተገነባው የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ የኅብረተሰቡን ሕይወት በመለወጥ በኩል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል። የወረዳው ነዋሪዎች እንደተናገሩት፣ ከዚህ ቀደም ለወፍጮ አገልግሎት ከ25 ኪሎ ሜትር በላይ ለመጓዝ ይገደዱ እንደነበር ገልፀው አሁን ግን በመኖሪያ አከባቢዎቻቸው አገልግሎቱን ማግኘት በመቻላቸው ተደስተዋል። በተለይም የኤሌክትሪክ አገልግሎቱን በቤት ውስጥ ከመጠቀማቸው ባሻገር እስከ ትምህርት ቤቶችና ጤና ተቋማት ድረስ በመድረሱ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል። ፕሮጀክቶቹ ከአንድ ዓመት ከስድስት ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ በ800 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ተጠናቀው የተገነቡ ሲሆን፣ በአጠቃላይ ከ931 ኪሎ ዋት በላይ ኃይል የማመንጨት አቅም እንዳላቸው ተገልጿል።    
በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በየመስኩ ስኬታማ ስራዎችን ለማከናወን ተችሏል
Aug 17, 2026 100
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በማሕበራዊ እና ኢኮኖሚ መስኮች ስኬታማ ስራዎች መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ አለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። የክልሉ ምክር ቤት 5ኛ የሥራ ዘመን 10ኛ መደበኛ ጉባኤ የ2018 በጀት ዓመት የልማትና የመልካም አስተዳደር አፈጻጸም ሪፖርትን አዳምጧል።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድ ሪፖርቱን ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ የነበሩ ፈተናዎችን በመቋቋም በግብርና፣ በማዕድን፣ በትምህርትና በሌሎችም ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች አበረታች ውጤቶችን ማስመዝገብ ተችሏል። ከዚህ ውስጥም በ2017/18 የምርት ዘመን በመኸርና በበጋ መስኖ ልማት 229 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ የተለያዩ ሰብሎችን ማልማት መቻሉን ገልጸዋል። በቡና ልማት ዘርፍም በአርሶ አደሮችና በባለሀብቶች ከለማው 73 ሺህ 425 ሄክታር መሬት 53 ሺህ 756 ቶን ምርት መገኘቱን አብራርተዋል። በበጀት ዓመቱ በማዕድን ልማት ዘርፍ 6 ሺህ ኪሎ ግራም ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ ገቢ ለማድረግ ታቅዶ 7 ሺህ 098 ኪሎ ግራም ወርቅ ለማቅረብ መቻሉን ገልጸው አፈጻጸሙም ከእቅድ በላይ ነው ብለዋል። የትምህርት ፍትሐዊነትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ሥራዎችም በአንደኛ፣ በመካከለኛና በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች 157 ሺህ ተማሪዎችን የትምህርት ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም ተናግረዋል።   በጤና፣ በንጹሕ መጠጥ ውሃ እና በሌሎችም ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች የነበሩትን ፈተናዎች በመቋቋም በበጀት ዓመቱ አበረታች ተግባራት መከናወናቸውን በሪፖርቱ ጠቁመዋል።
ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ከማዕድን ተገቢው ገቢ እንዲገኝ በትምህርት፣ በምርምር እና በአቅም ግንባታ ዘርፍ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
Aug 17, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከማዕድን ተገቢውን ገቢ እንድታገኝ ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በትምህርት፣ በምርምር እና በአቅም ግንባታ ዘርፍ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አስታወቀ፡፡ የማዕድን ዘርፍ ለአጠቃላይ የኢኮኖሚ ዕድገት እና ለውጭ ምንዛሬ ግኝት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲያበረክት ተለይቶ ትኩረት የተሰጠበት ሲሆን ዘርፉን ለማዘመንና አቅሙን ለማሳደግ በቴክኖሎጂ፣ በጥናትና ምርምር እንዲሁም በባለሙያ ስልጠና ላይ በርካታ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። በተጨማሪም የአካባቢውን ማህበረሰብ ከባህላዊ ወደ ዘመናዊ አሰራር በማሸጋገር፣ ዘላቂና ጤናማ የማዕድን ማውጣት ሂደትን ለመገንባት ጥረት እየተደረገ ነው። ቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ በማዕድን፣ በሀገር በቀል እውቀቶች፣ በግብርናና እንስሳት ሀብት እንዲሁም በጤና ዘርፎች ላይ አተኩሮ እየሰራ ይገኛል፡፡ በዩኒቨርሲቲው የስነ-ምድር እና ማዕድን ትምህርት ክፍል ኃላፊ አቶ ሙስጠፋ መሐመድ እንደገለጹት፣ ዩኒቨርሲቲው በአሁኑ ወቅት በዲግሪ እና በማስተርስ ደረጃ በማይኒንግ እና በጂኦሎጂ ትምህርት ተማሪዎችን እያስተማረ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ ከማስተማር ስራ ባሻገርም በጥናትና ምርምር የማህበረሰቡን ችግር ለመፍታት በማዕድን ዘርፍ ላይ የተለያዩ ጥናቶችን እያካሄደ መሆኑን አስረድተዋል። ዩኒቨርሲቲው በሚገኝበት አካባቢ መልካምድራዊ አቀማመጥ በማዕድን የበለጸገ በመሆኑ፣ ይህም ዩኒቨርሲቲው በዘርፉ ላይ ልዩ ትኩረት እንዲያደርግ ካደረጉት ምክንያቶች አንዱ መሆኑን ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ ለመዓድን ዘርፍ ልዩ ትኩረት መስጠቷን ጠቅሰው፣ ከዘርፉ ማግኘት የሚገባትን ገቢ እንድታገኝ በትምህርት፣ በምርምር እና በአቅም ግንባታ ድጋፍ ዘርፍ የበኩሉን እየተወጣ ይገኛል ብለዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ዘመናዊ ባልሆነ መልኩ ሲካሄድ የነበረውን የማዕድን ስራ ለማዘመን፣ ስልጠናና የአቅም ግንባታ ድጋፍ በመስጠት ማህበረሰቡ ከባህላዊ ወደ ዘመናዊ አሰራር እንዲሸጋገር የሚያስችሉ ስልጠናዎችን እየሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ምክትል ፕሬዚዳንት ገበየሁ አሻግሬ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፣ ዩኒቨርሲቲው ለማዕድን ዘርፍ ልዩ ትኩረት በመስጠት ተገቢ ፕሮግራሞችን ቀርፆ እየሰራ ይገኛል። ማዕድን በኢንስቲትዩት ደረጃ ራሱን ችሎ እንዲደራጅ ላቦራቶሪዎችን የማደራጀት፣ ልምድ ያላቸውን መምህራን የማሰባሰብ እና ከተለያዩ ትላልቅ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር በጋራ በመስራት መማር ማስተማር፣ ምርምር እና የማህበረሰብ አገልግሎት በትብብር እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም ዘመናዊ ላቦራቶሪ መደራጀቱን ጠቁመው፣ ሀገር ከአካባቢው ልታገኝ የሚገባትን ጥቅም እንድታገኝ በመማር ማስተማር እና በምርምር ስራ ላይ በጋራ እየሰሩ መሆናቸውን አስረድተዋል።   የቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ተመስገን ደበሎ (ዶ/ር) በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው ማዕድንን እንደ አንድ ትኩረት አቅጣጫ አድርጎ እንዲሰራበት መንግስት የፈለገበት ዋነኛ ምክንያት የጉጂ አካባቢ በርካታ ማዕድናት የሚገኙበት በመሆኑ ነው ብለዋል። ለዚህም ነው ዩኒቨርሲቲው ማዕድንን እንደ ዋና የትኩረት አቅጣጫ አድርጎ የሚሰራው ብለዋል።
በአፍሪካ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ለዘር ባንኮች መጠናከርና ለማዳበሪያ ምርት ትኩረት መስጠት ይገባል
Aug 17, 2026 125
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦በአፍሪካ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ለሀገር በቀል ዝርያዎች ጥበቃ የሚሆኑ የዘር ባንኮች መጠናከርና ለማዳበሪያ ምርት ዕድገት በትኩረት መስራት እንደሚገባ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ጥበቃ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ ገለፁ። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) አባል ሀገራት የግብርና ትራንስፎርሜሽን አፈፃፀም ግምገማ እና ከ2026 እስከ 2035 በሚተገበረው የካምፓላ ድንጋጌ ማዕቀፍን አስመልክቶ በአዲስ አበባ ምክክር መካሄድ ጀምሯል። ከዛሬ ነሃሴ 11ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ቀናት በሚቆየው የምክክር መድረክ አምስተኛው አጠቃላይ የአፍሪካ የግብርና ልማት መርሐ-ግብር (CAADP) የሁለት ዓመት አፈፃፀም ሪፖርትንና የኢጋድን ቀጣናዊ አፈፃፀም ይገመግማል። በመድረኩ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ጥበቃ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ አፍሪካ 60 በመቶ ያልታረሰ ለም መሬት እያላት በየዓመቱ ከ100 ቢሊዮን ዶላር በላይ የምግብ ምርትን ከውጭ ለማስገባት ታወጣለች ብለዋል። የማላቦ የሁለት ዓመት ግምገማ ዘመን ማብቃቱን አንስተው፣ የቀጣይ ትኩረት ውጤታም ትግበራ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። አፍሪካ በካምፓላ አጀንዳ አማካኝነት እስከ 2035 የግብርና ምርትን በ45 በመቶ፣ በአህጉር ውስጥ የሚደረግ ንግድን በሶስት እጥፍ ማሳደግ፣ ከምርት ስብሰባ በኋላ የሚባክነውን ምርት በ50 በመቶ መቀነስ እና 100 ቢሊዮን ዶላር ኢንቨስትመንት የማሰባሰብ ግብ መቀመጡን ገልጸዋል። እነዚህን ግቦች ለማሳካት የአፈር ጤናማነት፣ የሀገር በቀል ዝርያዎችን የሚጠብቁ የዘር ባንኮችን ማጠናከር እና አፍሪካ ያላትን የፎስፌትና ፖታሽ ሃብት በመጠቀም ማዳበሪያን በራሷ የማምረት ስራ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባ ተናግረዋል። የካምፓላ አጀንዳ ስኬት የሚለካው በአህጉሪቱ ዜጎች ህይወት ላይ በሚያመጣው ለውጥ መሆኑንም አስገንዝበዋል። የምስራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የግብርና እና አካባቢ ጥበቃ ዲቪዥን ዳይሬክተርን በመወከል ንግግር ያደረጉት ሲልቪያ ሄንጋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ግጭት፣ የካርቦን ልቀት፣ የአየር ንብረት ለውጥና መፈናቀል የግብርናውን ዘርፍ እየጎዳ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣናው የመስኖ አጠቃቀም ከ20 በመቶ በታች መሆኑንና ኢጋድ የአፈር መረጃ ስርዓትና የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓቶችን እየተገበረ መሆኑን አስታውቀዋል። የግብርና ሚኒስትር አማካሪና የመርሃግብሩ የኢትዮጵያ ተወካይ ዜና ሀብተወልድ ኢትዮጵያ የካምፓላ አጀንዳን ወደ ሀገር በቀል አሰራር ለመቀየር ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር እየሰራች መሆኑን አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅት ሀገሪቱ የሌማት ትሩፋትን ጨምሮ ለዘርፉ የጎላ አስተዋፅኦ ያላቸው መርሃ ግብሮችን በመተግበር ላይ እንደምትገኝም ገልጸዋል።
በኢሉባቦር ዞን በኩታ ገጠም ከለማው የበቆሎ ሰብል የተሻለ ምርት ለማገኘት የእንክብካቤ ስራ ተጠናክሯል
Aug 17, 2026 111
መቱ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በኢሉባቦር ዞን በክረምት እርሻ እየለማ ከሚገኘው የበቆሎ ሰብል የላቀ ምርት ለማገኘት የሰብል እንክብካቤና ጥበቃ ስራ በተቀናጀ ሁኔታ እየተከናወነ ይገኛል። የኦሮሚያ ክልል ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና ምርታማነትን ለማሳደግ የ"ኩታ ገጠም" የእርሻ ዘይቤን በስፋት በመተግበር ላይ ይገኛል። በክልሉ በክረምት ወቅት እንደ በቆሎ፣ ስንዴ፣ እና ጤፍ ያሉ ዋና ዋና ሰብሎች በስፋት ይመረታሉ። በቆሎ ለሀገር ውስጥ የምግብ ፍጆታ ብቻ ሳይሆን ለእንስሳት መኖ እና ለኢንዱስትሪ ጥሬ ዕቃነት ከፍተኛ ሚና ስላለው፣ በዘመናዊ አሰራር እና በኩታ ገጠም ዘዴ ምርታማነቱን ማሳደግ የክልሉ ዋና የልማት ግብ ነው። ከኦሮሚያ ክልል ዞኖች አንዱ የሆነው ኢሉባቦር ዞን በተለይም ለጥራጥሬ እና ለበቆሎ ሰብል ልማት እጅግ ተስማሚ የአየር ንብረት ያለው በመሆኑ፣ በአካባቢው የሚገኙ አርሶ አደሮች በክረምት ወቅት በቆሎን በስፋት ያመርታሉ። በዚሁ መሰረት በዞኑ በሁሩሙ ወረዳ በኩታ ገጠም የበቆሎ ልማት ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች እንደገለጹት፣ የታቀደውን ከፍተኛ ምርት ለማሳካት አረም የማረም፣ ኩትኳቶና የሰብል ጥበቃ ስራዎችን በትኩረት ያከናውናሉ። በዞኑ የሁሩሙ ወረዳ አርሶ አደር መብሬ አለነ እንደተናገሩት፤ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመቀናጀት በቆሎን በኩታ ገጠም እያለሙ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ ለሰብሉ የሚያደርጉት ጥንቃቄና እንክብካቤ አሁን ላይ ሰብሉ በጥሩ ቁመና ላይ እንዲገኝ ማስቻሉን ተናግረዋል። የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ይመር ከበደ በበኩላቸው መሬት ማረስና ዘር መዝራት ብቻ በራሱ ለውጤት እንደማያበቃ ተናግረው፤ በዚህም የሰብል ጥበቃና እንክብካቤ ስራ ወሳኝ ነው ብለዋል። በመሆኑም በባለሙያ እገዛ በኩታ ገጠም ከለማው ማሳቸው የተሻለ ምርት ለመሰብሰብ የሰብል እንክብካቤና ጥበቃ ስራውን ቤተሰቦቻቸውን በማሳተፍ በትጋት እየሰሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል። የኢሉባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ዳኜ ፍቅሬ እንደገለጹት፤ በዞኑ በክረምቱ ወቅት ከ389 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች እየለማ ሲሆን፣ ከዚህ ውስጥ 95 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በበቆሎ ሰብል የተሸፈነ ነው። በልማቱ ውጤታማ እንዲሆኑ ለአርሶ አደሮቹ የግንዛቤ ስልጠና መሰጠቱን ጠቅሰው፤ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በወቅቱ መቅረባቸውን ተናግረዋል። በበቆሎ ሰብል ከተሸፈነው 95 ሺህ ሄክታር መሬት የታቀደውን 4 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ከእርሻ ዝግጅት ጀምሮ እስከ ምርት ስብሰባ ባለው ሂደት አርሶ አደሩ የሰብል ጥበቃ ስራዎችን በተቀናጀ መልኩ እንዲያከናውን እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በአጠቃላይ የክረምት እርሻ ልማቱን ውጤታማ ለማድረግ ሙያዊ ድጋፍና የክትትል ሰራዎች ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን አብራርተዋል።    
የፀሃይ ሃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱ ለረጅም ጊዜ የልማት ጥያቄያችን ምላሽ የሰጠ ነው- የቁምቢ ወረዳ ነዋሪዎች
Aug 17, 2026 120
ቁምቢ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦ የፀሃይ ሃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱ ለረጅም ጊዜ የልማት ጥያቄያችን ምላሽ የሰጠ ነው ሲሉ በምስራቅ ሐረርጌ ተናገሩ። በወረዳው ሀሮ ጉራቲ እና ሀሪሮ ቀበሌዎች በ640 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነቡ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች ሰሞኑን ተመርቀው ለአገልግሎት በቅተዋል። ፕሮጀክቶቹ ተመርቀው አገልገሎት መጀመራቸው በአካባቢው በተደጋጋሚ የነበረውን የሃይል መሰረተ ልማት ጥያቄ መሰረት ያደረገ ሲሆን ነዋሪዎች የኤሌክትሪክ ሃይል ተጠቃሚ በመሆናቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። በቁምቢ ወረዳ የሃሪሮ ቀበሌ ነዋሪዎች መካከል መምህር ማዕሩፍ አብደላ እና ወይዘሮሂ ክማ ቀመር፤ የኤሌትሪክ ሃይል አቅርቦት ባለመኖሩ ለአገልግሎትና የልማት ስራዎች ጭምር ማነቆ ሆኖ መቆየቱን አንስተዋል። በመሆኑም የኃይል ልማት የማህበረሰቡ የረጅም ጊዜ ጥያቄ እንደነበር አስታውሰው፤ ምላሽ በማግኘቱና መሰረተ ልማቱ በመሟላቱ ተደስተናል ብለዋል። የፀሃይ ሃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱ ለረጅም ጊዜ የልማት ጥያቄያችን ምላሽ የሰጠ ነው ሲሉም ተናግረዋል። የፀሐይ ኃይል አገልግሎት በመጀመሩ በተለይም ለትምህርት ተቋማት ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን ያነሱት መምህር ማዕሩፍ፤ ለተሻለ የትምህርት አሰጣጥና ተደራሽነት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በአካባቢያቸው የፀሐይ ኃይል አገልግሎት ከተጀመረ ወዲህ ግን በዳቦ በማምረትና ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኙ ያነሱት ደግሞ የቀበሌው ተወላጅ ወይዘሮሂ ክማ ቀመር ናቸው። በመሆኑም በተሰማሩበት የምግብ ቤትና የዳቦ የማምረት ስራ ውጤታማ ለመሆን በትጋት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። የሐሪሮ ሆስፒታል ጠቅላላ ሀኪም ዶክተር አፈንዲ አልይ፤ በአካባቢው የሃይል መሰረተ ልማት ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱ በተለይም ለማህበራዊ አገልገሎትና አጠቃላይ ለኢኮኖሚ ልማት ብዙ ትርጉም ያለው ነው ብለዋል። ለአብነትም ሆስፒታሉ ቀደም ሲል ውስን ሰዓት የሚሰጠውን የህክምና አገልግሎት ወደ 24 ሰዓት እንዲያድግ እንዲሁም የላብራቶሪና የራጅ አገልግሎት በተሻለ መልኩ ለመስጠት ያስችላል ብለዋል። የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሡልጣን ወሊ (ዶ/ር)፤ በተለይ በተቀናጀ የውሃ ሃብት አስተዳደር፣በንጹህ መጠጥና ሳኒዬሽና በሃይል አቅርቦት በተከናወነው ተግባራት አመርቂ ውጤቶች ተመዝግበዋል ብለዋል። የተመረቁት የኃይል ልማት ፕሮጀክቶች በድምሩ 900 ኪሎ ዋት ኃይል የማመንጨት አቅም እንዳላቸውና ከ4 ሺህ በላይ ዜጎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ መሆኑ ታውቋል።
በተቀናጀ ዐቅም ተግተን ከሠራን ብልጽግና ሕይወት፣ድህነት ታሪክ ይሆናል- ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Aug 16, 2026 396
አዲስ አበባ ፤ነሀሴ 10 /2018 (ኢዜአ)፦ለም አፈር፣ ንጹሕ ውኃና ሥራ ወዳድ ሕዝብ ባለበት ምድር፣ በተቀናጀ ዐቅም ተግተን ከሠራን ብልጽግና ሕይወት፣ ድህነት ታሪክ ይሆናል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለፁ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልእክት የሃይቅ ዙሪያ አርሷደሮች መሬት እና እርሻቸውን ከጫት ወደ አትክልት እና ፍራፍሬ ክላስተር አሸጋግረውታል ብለዋል። አርሷደሮቹ የአካባቢን አንጻራዊ የልማት ጉልበት መለየት እና ወደ አትራፊ እና ዘላቂ የግብርና ጎዳና መሸጋገር ይገባል የሚለውን ሃገራዊ መርህ እና ስምሪት ተግብረው አሳይተዋል ነው ያሉት። ከዚህ ቀደም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ምርቃት ላይ ባስተላለፉት ታሪካዊ መልዕክት "ሐይቅ የታሪክ ብቻ ሳይሆን የፍራፍሬ ልማት፣ የተትረፈረፈ ምርት፣ የውበትና የጥጋብ ሥፍራ መሆን አለባት" ማለታቸውን አስታውሰዋል። ዛሬ የርሳቸው ቃል ፍሬ አፍርቶ በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን፣ ተሁለደሬ ወረዳ የጎበያ ቀበሌ በአትክልት እና ፍራፍሬ ክላስተር ተሸፍኗል። ይህ የልማት ትጋት ኢትዮጵያ ለጀመረችው የምግብ ሉዓላዊነት ተደማሪ ጥሪት እና ወረት ነው ሲሉ ጠቁመዋል። መንግሥት ለዚህ ልማት አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረጉን ይቀጥላል ያሉ ሲሆን ለም አፈር፣ ንጹሕ ውኃና ሥራ ወዳድ ሕዝብ ባለበት ምድር፣ በተቀናጀ ዐቅም ተግተን ከሠራን - ብልጽግና ሕይወት፣ ድህነት ታሪክ እንደሚሆን ገልጸዋል።
በአማራ ክልል የሚገኙ ከተሞችን በፕላን ለመምራት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው-ኢንስቲትዩቱ 
Aug 16, 2026 146
ጎንደር ፤ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የሚገኙ ከተሞችን ዘላቂ ልማት ለማረጋገጥ የሚያስችል ፕላን ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ፕላን ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ያለፈው ዓመት አፈጻጸም፣ የ2019 ዕቅድ ትውውቅና የተለያዩ የሕግ ማዕቀፎችን መሠረት ያደረገ የውይይት መድረክ በጎንደር ከተማ እያካሄደ ነው።   በውይይቱ ላይ የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዳይሬክተር ተስፋሁን ተናኜ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ ከተሞች ለነዋሪዎቻቸው ምቹ፣ ተወዳዳሪና ዘላቂ ልማት የሚያረጋግጡ እንዲሆኑ እየተደረገ ነው። ከዚህ ውስጥም የከተሞችን ዕድገት ለማፋጠን በየደረጃው መዋቅራዊ ፕላን በማዘጋጀት እስካሁን ከ137 በላይ ለሚሆኑ ከተሞች የፕላን ዝግጅት ተከናውኗል። በተጨማሪም፣ ከ31 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የግንባታ ጥያቄዎች በከተሞች ፕላን መሠረት መከናወናቸውን ማረጋገጥ ተችሏል። ይህም በከተሞች የመንገድ፣ የውኃ፣ የመብራትና ቴሌኮም የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እንዲሳለጡ የሚያደርግ መሆኑን አስገንዝበዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም የተጀመሩ ተግባራትን በማጠናከር፣ የከተሞችን ዕድገትና ዘመናዊነት የሚያረጋግጡ ዕቅዶች ተግባራዊ ይደረጋሉ ነው ያሉት። በክልሉ ፕላን ኢንስቲትዩት የጎንደር ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ግዛቸው አዳነ በበኩላቸው፣ የከተሞች ፕላን ክለሳ፣ የመዋቅራዊና መሠረታዊ ፕላን ዝግጅት እና የሰፈር ልማት ፕላን ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቱ በማዕከላዊ ጎንደር፣ በምዕራብ ጎንደር እና በሰሜን ጎንደር ዞኖች ሥር የሚገኙ ከተሞችን በመከታተል የፕላን ዝግጅትና ትግበራ ድጋፍ እያደረገ ነው ብለዋል። ከዛሬ ጀምሮ ለሦስት ቀናት በሚካሄደው በዚህ መድረክ ላይ የኢንስቲትዩቱ የሥራ ኃላፊዎችና የቅርንጫፍ አመራሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።  
የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተተገበሩ የፖሊሲ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው - ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር)
Aug 16, 2026 434
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፦የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተተገበሩ የፖሊሲ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የግብርናውን ዘርፍ ውጤታማነት ለማሳደግ ተግባራዊ የተደረጉ የፖሊሲ እርምጃዎች ተጨባጭ ውጤቶች እያመጡ ነው። የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል የተመቻቹ የፋይናንስ አቅርቦት ዕድሎች የግል ባለሀብቶችን ተሳትፎ እያሳደጉ መምጣታቸውንም ገልጸዋል። ይህም የግሉ ዘርፍ በፋይናንስ፣ በቴክኖሎጂና በሌሎች የትብብር መስኮች የሚያደርገውን ተሳትፎ ለማጎልበት ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊ የግብርና ግብዓቶችና ሜካናይዜሽን በሰፊው ጥቅም ላይ እንዲውሉ መደላድል በመፈጠሩም የምርት መጠንና ጥራት እያደገ መምጣቱን አስረድተዋል። የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥም በማዳበሪያ አቅርቦት ላይ ያለውን ጥገኝነት በሀገር ውስጥ አቅም ለመተካት የሚያስችል የማዳበሪያ ፋብሪካ በግንባታ ሂደት ላይ መሆኑን አንስተዋል።   የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአምስት ዓመታት ጊዜ የታረሰውን መሬት በሦስት እጥፍ ማሳደግ እንደተቻለ አስረድተዋል። በዚህም በሰብልና በእንስሳት ሃብት ልማት ምርታማነትን ጨምሮ በሁሉም የግብርና ዘርፎች የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል እምርታዊ ዕድገት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል። የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥም ከሀገር ነፃነትና ደህንነት ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት ያለው ቁልፍ ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ ዐሻራ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቀነስ ለግብርና ምርታማነት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እያስገኘ ነው ብለዋል። ይህም የግብርናውን ትራንስፎርሜሽን ውጤታማነት በማጎልበት የምግብ ዋስትና እንዲረጋገጥ መሠረት ከመጣል ባሻገር በሥራ ዕድል ፈጠራም የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩ የሀገር ውስጥ ፍጆታን ከመሸፈን ባለፈ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶች እየተገኙበት ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታዋ፤ የውጭ ምንዛሬ ግኝትም እንዲጨምር እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አረንጓዴ ዐሻራ የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በማስጠበቅ በካርቦን ሽያጭ ጭምር ገቢ መፍጠር እያስቻለ ነው ብለዋል። ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ሥርዓት ለመገንባት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑንም ገልጸዋል።  
የአዲስ አበባን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የፍሳሽ ማጣሪያ አቅም የሚያጎለብት ውጤታማ ሥራ እየተሠራ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Aug 16, 2026 361
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት እና የፍሳሽ ማጣሪያ አቅም የሚያጎለብት ውጤታማ ሥራ እየተሠራ መሆኑን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአራብሳ አካባቢ የተገነባውን የንጹህ መጠጥ ውሃ መሠረተ ልማትና የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።   ከንቲባዋ በዚሁ ወቅት፣ ፕሮጀክቱ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትን በጉልህ እንደሚያሳድግ ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት የንጹህ የመጠጥ ውሃ እጥረትን ለመፍታት የተከናወኑ ሥራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ የመዲናዋ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት በቀን ከ910 ሺህ ሜትር ኪዩብ በላይ መድረሱን አስታውቀዋል። በቀጣይም ከፍተኛ የማምረት አቅም ያላቸው የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ እንደሚገቡ ተናግረዋል። በሌላ በኩል የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ የሕብረተሰቡን ጤናና የአካባቢ ጥበቃን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ከንቲባዋ ገልጸዋል። ጣቢያው ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም መሆኑን በማንሳት፣ መሰል የፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያዎችን በስፋት ለመገንባት መታቀዱን አስረድተዋል። መሠረተ ልማት መገንባት ብቻውን ግብ አይደለም ያሉት ከንቲባ አዳነች፤ የተገነቡትን መሠረተ ልማቶች መጠበቅና መንከባከብ የሁሉም የጋራ ኃላፊነት ሊሆን እንደሚገባ አስገንዝበዋል። አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ከተማ ለማድረግ የተጀመሩት የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በማንሳት፣ ለፕሮጀክቶቹ እውን መሆን አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል።   የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ዘሪሁን አባተ በበኩላቸው፤ የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ በቀን 20 ሺህ ሜትር ኪዩብ የማጣራት አቅም እንዳለው ገልጸዋል። ጣቢያው የከተማዋን የፍሳሽ ማጣራት አቅም በከፍተኛ ሁኔታ የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል። የከተማዋን እድገት የሚመጥኑ የመጠጥ ውሃና የፍሳሽ ማጣሪያዎች በተለያዩ አካባቢዎች እየተገነቡ መሆናቸውን አንስተዋል። የዛሬው ቀን የፕሮጀክት መጠናቀቅን ብቻ የሚያሳይ አይደለም ያሉት ደግሞ በአለም ባንክ ምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ሪጅን፣ የኢትዮጵያ፣የሱዳን፣ ደቡብ ሱዳን እና ኤርትራ ተወካይ ዲቪዥን ዳይሬክተር ራጁል አዋስቲ ናቸው።   የኮዬ የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ጣቢያ አዲስ አበባ ንፁህ፣ ጤናማ እና የተሻለች ከተማ ለመሆን የምታደርገው ጉዞ ታሪካዊ ምዕራፍ መሆኑን ጠቁመዋል። የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ የከተሞች የውሃ እና ሳኒቴሽን ዘርፍ የሚያደርገው ተሳትፎ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ያለውን የረጅም ጊዜ እና ከፍተኛ ዋጋ የሚሰጠውን አጋርነት የሚያንጸባርቅ መሆኑን ተናግረዋል።  
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ተጨማሪ ሃብት ለማፍራት አስችሎናል-ተጠቃሚዎች
Aug 16, 2026 172
ጎንደር፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ) ፡-የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ኑሯቸውን ለመለወጥና ተጨማሪ ሀብት ለማፍራት እንዳስቻላቸው በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ተጠቃሚዎች ገለጹ። የሌማት ትሩፋት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የሥነ-ምግብ ደረጃን ለማሻሻልና አጠቃላይ የግብርና ምርታማነትን በጥራትና በብዛት ለማሳደግ ያለመ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው። መርሃ-ግብሩ በተለይም በወተት፣ በማር፣ በዶሮ እርባታ፣ በሥጋ እንዲሁም በጓሮ አትክልትና ፍራፍሬ ልማት ላይ ትኩረት በማድረግ የቤተሰብ ገቢን ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። በወገራ ወረዳ አምባ ጊዮርጊስ ከተማ በዶሮ እርባታ ሥራ የተሰማሩት አቶ አበራ ምስጋናው ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር በመታቀፍ በ1 ሺህ ጫጩቶች የጀመሩትን ሥራ በርትተው በመስራት የተሻለ ገቢ ማግኘት ጀምረዋል።   ሥራቸውን በማስፋፋትም አሁን ላይ በአንድ ጊዜ እስከ 3 ሺህ የሚደርሱ ዶሮዎችን አሳድገው ለመሸጥ የሚያስችል አቅም መፍጠራቸውን ተናግረዋል። ሌላው የከተማዋ የ02 ቀበሌ ነዋሪ አቶ ማርየ ራራ በበኩላቸው፤ ከመንግሥት ሥራቸው ጎን ለጎን ባላቸው ትርፍ ጊዜ በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር መሳተፋቸው የቤተሰባቸውን ሕይወት ከመለወጡ ባለፈ ተጨማሪ ሀብት ለመፍጠር እንደቻሉ ተናግረዋል።   አስተያየት ሰጪዎቹ በተሰማሩበት የዶሮ እርባታ ሥራ ውጤታማ እንዲሆኑ ከአካባቢው አስተዳደር የተደረገላቸው የቦታና የብድር ድጋፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አብራርተዋል። የማዕከላዊ ጎንደር ዞን የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ ዶክተር ምስጋናው ታከለ በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ብቻ ለ20 ሺህ 588 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ተናግረዋል።   ዘርፉ ሥርዓተ-ምግብን ከማሻሻል ባለፈ ዜጎች የኑሮ ሁኔታቸውን እንዲለውጡና ሀብት እንዲፈጥሩ ማስቻሉንም አስረድተዋል።  
ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል የመንግስትና የህዝብ ሀብትን ከብክነት ማዳን ተችሏል
Aug 16, 2026 166
አዳማ፤ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፡- ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል የመንግስትና የህዝብ ሀብትን ከብክነት ማዳን መቻሉን የአዲስ አበባና የድሬዳዋ አስተዳደር ሥነ ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች አስታወቁ። የፌዴራል ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ያዘጋጀው 17ኛው ሀገር አቀፍ የሥነ-ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽኖች ትስስር ጉባኤ ትናንት በአዳማ ከተማ ተካሂዷል። የአዲስ አበባ ከተማ ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽነር ጀማል ረዲ በዚሁ ወቅት ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብልሹ አሰራሮችን በመከላከል የመንግስትና የህዝብ ሀብትን ከብክነት ለማዳን ሰፋፊ ስራዎች ተከናውነዋል። ከዚህ ውስጥም ኮሚሽኑ በአስቸኳይ ሙስና መከላከል የሥራ ዘርፍ ከሕዝብ የቀረቡለትን 290 ጥቆማዎች ተቀብሎ በመመርመር፣ 80 በመቶ የሚሆኑት የሙስና ይዘት እንዳላቸው ማረጋገጡን ገልጸዋል። ይህንን ተከትሎ በተወሰደው እርምጃ በአስቸኳይና በመደበኛ ሙስና መከላከል ተግባራት በአጠቃላይ ከ706 ሚሊዮን ብር በላይ ከምዝበራ ማዳን ተችሏል ነው ያሉት። ከገንዘብ በተጨማሪም 8 ሺህ 103 ካሬ ሜትር መሬት በማዳን ወደ መሬት ባንክ ገቢ እንዲሆን መደረጉን ተናግረዋል። ብልሹ አሰራሮችንና ሙስናን የመከላከል እርምጃዎችን ለማጠናከር የጥቆማ ሥርዓቱ ዘመናዊና ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሆን የጥሪ ማዕከል የማደራጀት እና ጥቆማዎች በዘመናዊ ዳታቤዝ እንዲያዙ የማድረግ ስራ መሰራቱን ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ በመዲናዋ በበጀት ዓመቱ በትውልድ ሥነ-ምግባር ግንባታና በሙስና መከላከል በኩል ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቁመዋል። በተለይም የፀረ-ሙስና ትግሉን ከማጎልበት አንጻር የተለያዩ መድረኮችን በማዘጋጀት ለ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን የኅብረተሰብ ክፍሎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና መሰጠቱን አስታውቀዋል።   የድሬዳዋ አስተዳደር የሥነ-ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽነር አቶ ፌኑስ አብዱልጀባር በበኩላቸው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተለያዩ ተቋማት ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከል የሚያስችል ጥናት መካሄዱን ገልጸዋል። በተለይም በአስቸኳይ ሙስና መከላከል በተደረገው ጥረት በድሬዳዋ አስተዳደር ድሬ ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ፤ የፔዳጎጂካል ቴክኖሎጂ፣ ኮምፒዩተር እና ተያያዥ አክሰሰሪዎች ግዥ ጨረታ ግልጽነት የጎደለው ሆኖ መገኘቱን ለአብነት አንስተዋል። የግዥ ጨረታው ህጋዊ አሰራርን ያልተከተለና ውስንነት ያለበት በመሆኑም ሂደቱ ተቋርጦ፣ ተስተካክሎና ህጋዊ አሰራርን ተከትሎ እንዲቀጥል መደረጉን ተናግረዋል። አስተዳደሩ የሙስና ትግሉን ህዝባዊ መሰረት ለማስያዝ በተለያዩ አማራጮች ግንዛቤ ለመፍጠር እየሰራ መሆኑን አመልክተው፤ ህብረተሰቡ ሙስና እና ብልሹ አሰራርን ሲመለከት ጥቆማ በመስጠት ረገድ የተሻለ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው ብለዋል።  
በአፋር ክልል የገቢ አማራጮችን የማስፋትና በቁርጠኝነት ገቢን የመሰብሰብ ተግባራት ይጠናከራሉ
Aug 16, 2026 122
ሰመራ፣ነሀሴ 10/2018 (ኢዜአ):- በአፋር ክልል በተያዘው በጀት ዓመት የገቢ አማራጮችን የማስፋትና በቁርጠኝነት ገቢን የመሰብሰብ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ ገለጹ። የተጠናቀቀው በጀት ዓመት አፈፃፀምና የ2019 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ የሥራ ኃላፊዎች የተገኙበት የውይይት መድረክ በሰመራ ተካሄዷል።   በውይይት መድረኩ ማጠቃለያ ላይ የተገኙት ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እንደተናገሩት፣ የክልሉን ልማት ለማቀላጠፍና የህብረተሰብ ጥያቄዎችን ለመመለስ ገቢን በአግባቡ መሰብሰብ ከፍተኛ ሚና አለው። ርዕሰ መስተዳድሩ አክለውም፣ በተያዘው በጀት ዓመት በክልሉ የገቢ አማራጮችን የማስፋትና በቁርጠኝነት ገቢን የመሰብሰብ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። ከዓመት ወደ ዓመት ገቢን የመሰብሰብ አቅም እየጨመረ መምጣቱን ገልጸው፣ ከለውጡ በፊት የነበረውን 790 ሚሊዮን ብር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ወደ 8 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል። የመሰብሰብ አቅምን በማሳደግ በጀትን በራስ አቅም ለመሸፈን የሚደረገው ጥረት እየተጠናከረ መምጣቱን ገልጸው፣ በተለይም አመራሩ ኃላፊነቱን በአግባቡ ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል። መተባበርንና መትጋትን ማዕከል በማድረግ የታቀደውን ዕቅድ ለማሳካት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አብራርተዋል። በያዝነው ዓመት ደግሞ የገቢ ግብርን ከፍ በማድረግ ከ16 ቢሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ የተገባ መሆኑን ገልጸው፣ ለዚህ ስራ ስኬታማነት በየደረጃው ያለው አመራር የድርሻውን መወጣት እንዳለበትም አስገንዝበዋል። በተያዘው በጀት ዓመት ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ ለሕዝብ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ የመስጠቱ ተግባርን ማጠናከር ከሁላችንም ይጠበቃል ያሉት ደግሞ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ አቶ አወል አብዱ ናቸው። የሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢንጂነር አህመድ ኑር ሳሊም በበኩላቸው፣ የከተማዋን የገቢ አቅም የመለየት ስራዎች መከናወናቸውንና ለፈጻሚ ባለሙያዎች ትጥቅ የሚሆናቸው ስልጠናና የልምድ ልውውጥ መካሄዱንም በመድረኩ ገልጸዋል።   በመርሃ ግብሩ ማጠቃለያ ላይ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ የተሻለ አፈፃፀም ላስመዘገቡ ከተማ አስተዳደሮችና ወረዳዎች የእውቅና እና የሽልማት ስነ-ስርዓት አከናውነዋል።        
የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ልማት ዕድገትን የሚያፋጥን አስደማሚ ውጤት እያመጣ ነው - ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ምሁራን
Aug 16, 2026 394
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 10/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ብዝኅ የኢኮኖሚ ልማት ዕድገትን የሚያፋጥን አስደማሚ ውጤት እያመጣ መሆኑን የአሜሪካ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ምሁራን ገለጹ። አሜሪካዊው ፕሮፌሰር ኤድዋርድ ሚጉኤል እና ካሜሩናዊው የኢኮኖሚክስ ፕሮፌሰር ሊነስ ኒውል ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በተለያዩ ዘርፎች አስደናቂ ዕድገትና ለውጥ አስመዝግባለች። በአሜሪካ የካሊፎርኒያ በርክሌይ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ ፕሮፌሰር ኤድዋርድ ሚጉኤል፣ ከዘጠኝ ዓመታት በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ሲመለሱ በአዲስ አበባ የተመለከቱት ለውጥ እጅግ የሚያስደምም መሆኑን ገልጸዋል። የአዲስ አበባ አስደናቂ የከተሜነት ዕድገትና የልማት ለውጥ ከዚህ ቀደም ያውቋቸው የነበሩ አካባቢዎችን ገጽታ በእጅጉ በመቀየሩ እንደገና ለመለየት እንኳን እንደተቸገሩ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት ለከተማ መሠረተ ልማት የሰጠው ልዩ ትኩረት የኢኮኖሚ ዕድገትን በማፋጠን መሠረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑንም ገልጸዋል። በከተማ ልማት፣ በኢኮኖሚ ማሻሻያና በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም የተመዘገቡ ውጤቶች የኢትዮጵያን የልማት ቁርጠኝነት የሚያሳዩ አስደናቂ ስኬቶች መሆናቸውን አንስተዋል። ኢትዮጵያ በብዝኅ ኢኮኖሚ ዘርፎች የወሰደቻቸው የፖሊሲ ማሻሻያ እርምጃዎችም ዕድገትን በማፋጠን አዎንታዊ ውጤት እያመጡ እንደሚገኙ አንስተዋል። በአየር ንብረት ለውጥ ረገድም ኢትዮጵያ አዳዲስ የማኅበራዊ ፕሮግራሞችንና የፋይናንስ አሠራሮችን በመዘርጋት የመቋቋም አቅሟን ለማሳደግ የወሰደቻቸው እርምጃዎች የሚደነቁ መሆናቸውን ጠቁመዋል። አፍሪካ ለድርቅና ለጎርፍ ተጋላጭ በሆነችበት በዚህ ወቅት የመንግሥት ቁርጠኝነትና በዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ ጥረቶች እጅግ አስፈላጊ መሆናቸውንም አብራርተዋል።   በአሜሪካ ፔንሲልቬኒያ ጌቲስበርግ ኮሌጅ የኢኮኖሚክስ ምሁር የሆኑት ካሜሩናዊው ፕሮፌሰር ሊነስ ኒውል በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች አስደናቂ ዕድገት እያስመዘገበች መሆኑን ገልጸዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የወሰደቻቸው አስደናቂ የልማት መርሃ ግብሮችም የሀገሪቱን ዕድገት ከማፋጠን ባሻገር አረንጓዴ የኢኮኖሚ አቅሞችን ለመገንባት የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚን በመገንባት እያስመዘገበች ያለችው እመርታም ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጭምር የሚተርፉ ወሳኝ ተሞክሮ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያ መንግሥት በአየር ንብረት ለውጥ መከላከልና መቋቋም ውጤታማነቱን በማሳደግ፣ አህጉራዊ የምሪት ሚናዋን አጠናክራ ልትቀጥል እንደሚገባ አስገንዝበዋል።  
አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Aug 16, 2026 209
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 10/2018(ኢዜአ)፦አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአራብሳ አካባቢ የተገነባውን የንጹህ መጠጥ ውሃ መሠረተ ልማትና የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። ከንቲባዋ በመርሃ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፣ ፕሮጀክቱ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትን በጉልህ እንደሚያሳድግ ገልጸዋል።   ባለፉት ዓመታት የመጠጥ ውሃ እጥረትን ለመፍታት የተከናወኑ ሥራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን ጠቅሰው፣የመዲናዋ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት በቀን ከ910 ሺህ ሜትር ኪዩብ በላይ መድረሱን አስታውቀዋል። በቀጣይም ከፍተኛ የማምረት አቅም ያላቸው የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ እንደሚገቡ ተናግረዋል። በሌላ በኩል የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ የሕብረተሰቡን ጤናና የአካባቢ ጥበቃን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ከንቲባዋ ገልጸዋል። ጣቢያው ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የሚጠቀም መሆኑን በማንሳት፣ መሰል የፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያዎችን በስፋት ለመገንባት መታቀዱን አስረድተዋል። መሠረተ ልማት መገንባት ብቻውን ግብ አይደለም ያሉት ከንቲባ አዳነች፣ የተገነቡትን መሠረተ ልማቶች መጠበቅና መንከባከብ የሁሉም የጋራ ኃላፊነት ሊሆን እንደሚገባ አስገንዝበዋል። አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ከተማ ለማድረግ የተጀመሩት የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በማንሳት፣ ለፕሮጀክቶቹ እውን መሆን አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በቀን 20 ሺህ ሜትር ኪዮብ ፍሳሽ የሚያጣራውን የኮዬ ፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ ፕሮጀክት አስመረቁ
Aug 16, 2026 184
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 10/2018(ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በቀን 60 ሺህ ሜትር ኪዮብ ንፁህ የመጠጥ ውሃ የሚያመርት እና በቀን 20 ሺህ ሜትር ኪዮብ ፍሳሽ የሚያጣራ የኮዬ ፍሳሽ ዘመናዊ ማጣሪያ ጣቢያ ፕሮጀክቶችን አስመርቀው አገልግሎት አስጀምረዋል። ንጹህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ለማሳደግ በቱሉ ጉዶ፣ ለገዳዲ ክፍል 2፣ በረከት የጋራ መኖሪያ አካባቢ፣ ቦሌ አራብሳና ሌሎችም በርካታ ጉድጓዶችን በማልማት በከተማዋ ከአምስት ዓመት በፊት የነበረው 525 ሺህ ሜትር ኪዩብ በቀን የማምረት አቅም ዛሬ ላይ 910 ሺህ ሜትር ኪዩብ መድረሱን በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ጠቁመዋል፡፡   ፕሮጀክቶቹ የነዋሪዎቻችንን ጤናና ንጽህና የሚጠብቁ፣ የወንዞቻችንን ብክለት የሚቀንሱ፣ የአካባቢ ጥበቃችንን የሚያጠናክሩ ናቸው ብለዋል። አዲስ አበባን እንደ ስሟ አዲስ ውብ፣ ጽዱ፣ ጤናማ፣ አረንጓዴ፣ ዘመናዊና ለትውልድ የምትመች ከተማ ለማድረግ የጀመረው ግብ ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት።   ይህ ታላቅ ፕሮጀክት እውን እንዲሆን የብድር አገልግሎት ለሰጠው የዓለም ባንክ፣ እንዲሁም የውሃው መገኛ አካባቢዎችን በትብብር ለማልማት ላገዘው የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልል፣ ከሁሉ በላይ ዘላቂ ኑሯቸውን ሲመሩበት የነበረውን መሬት ለዚህ ታላቅ ልማት የለቀቁ አርሶ አደሮች እና ለፕሮጀክቱ ስኬት ሌት ተቀን ያለእረፍት የተጉ የውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን አመራሮች እና ባለሙያዎች ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
የአቮካዶ ልማትን በማዘመን ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል- ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር
Aug 16, 2026 250
ሐረር፣ ነሐሴ 10/2018 (ኢዜአ)፡- የአቮካዶ ልማትን በማዘመን ተጠቃሚነትን ለማሳደግ ትኩረት መደረጉን የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድ ሮዛ ኡመር ገለጹ። ሀገር አቀፍ የአቮካዶ ልማት ኢኒሼቲቭ ከሚተገበርባቸው 10 ክልሎች መካከል አንዱ የሐረሪ ክልል ሲሆን በዛሬው እለትም በገጠርና በከተማ ክላስተሮች የአቮካዶ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ተከናውኗል።   የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ ኡመር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የክልሉ መንግሥት በርካታ ኢኒሼቲቮችን ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ ነው። በአሁኑ ወቅትም አቮካዶን ጨምሮ ሌሎች የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሥራዎችን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ሰፊ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልፀዋል። የአቮካዶ ልማት ኢኒሼቲቭ ዋና ዓላማ ምርቱን በቴክኖሎጂ በማዘመን አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ከማድረግ ባሻገር ምርቱን ለውጭ ገበያ ማቅረብን ጨምሮ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥና የሥራ ዕድል መፍጠር ነው ብለዋል።   በተለይ የክልሉ የአየር ፀባይ ለአቮካዶ ልማት ምቹ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በክልሉ የግብርና ልማት ቢሮ የብሔራዊ የአቮካዶ ልማት ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ መሐመድ ሬድዋን ናቸው። በችግኝ ጣቢያዎች 106 ሺህ የተሻሻሉ የአቮካዶ ዝርያዎችን የማዘጋጀት ሥራ የተከናወነ ሲሆን፣ ችግኞቹን በገጠርና በከተማ በ100 ሄክታር መሬት ላይ ለማልማት መታቀዱን ገልጸዋል።   በችግኝ ተከላው ከተሳተፉት መካከል ወጣት ማሩፋ ሙሳ እና አርሶ አደር አብዲ በያን ፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የፍራፍሬ ችግኝ ተከላ ያስገኝውን ውጤት መነሻ በማድረግ አቮካዶን ይበልጥ ለማልማት መነሳሳታቸውን ነው የተናገሩት። አቮካዶ ልማት ሥራ ተጠቃሚነትን ከማጎልበቱ ባሻገር የሥራ ዕድል የሚፈጥር በመሆኑ በስፋት እየተሳተፉ እንደሚገኙም ነው ያመለከቱት።
በምዕራብ ጎንደር ዞን ከ172 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰሊጥና ማሾ ሰብል ለምቷል
Aug 16, 2026 103
ገንዳ ውኃ፣ ነሐሴ10/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን በመኸር እርሻ ከ172 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የሰሊጥና ማሾ ሰብሎችን ማልማት መቻሉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። ​የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የመምሪያው ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ዞኑ ለወጪ ንግድና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ የግብርና ምርቶችን በማምረት ላይ ይገኛል። በዚህም እስካሁን በተደረገው ጥረት በአጠቃላይ በሰሊጥና በማሾ ሰብል ከለማው ከ172 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ ከ169 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በሰሊጥ፣ ቀሪው ደግሞ በማሾ ሰብል መሸፈኑን ተናግረዋል።   ከዚህ ልማትም ከአንድ ነጥብ ሶስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስረድተዋል። ምርታማነቱን ለማሳደግም ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘርና የመካናይዜሽን አስተራረስ ዘዴዎችን በመጠቀም መዝራት መቻሉን ጠቁመዋል። በሰብል ልማቱ ከ59 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችና 500 የሚደርሱ ባለሀብቶች እየተሳተፉ መሆናቸውን ገልጸው፣ የአረምና የተባይ መከላከል ተግባራት በቅንጅት እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። ጥራቱን የጠበቀ ምርት ለገበያ ለማቅረብም በቅድመና ድህረ-ምርት አያያዝ ላይ ተገቢው ክትትልና ቁጥጥር እንደሚደረግ አብራርተዋል። በዞኑ የመተማ ወረዳ አርሶ አደር አቶ መሐመድ አህመድ በበኩላቸው፣ ዝናብ ዘግይቶ ቢጥልም የተገኘውን እርጥበት በመጠቀም አራት ሄክታር መሬታቸውን በሰሊጥ መሸፈናቸውን ተናግረዋል። በኩታ ገጠም አስተራረስና በዘመናዊ መካናይዜሽን ተጠቅመው ካለሙት ሰብልም ከ30 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። ሌላው የመተማ ወረዳ አርሶ አደር ደሳለኝ ገብሬ፣ በዘንድሮው የመኸር እርሻ የግብዓት አቅርቦት በወቅቱ መድረሱ ማሾና ሰሊጥን በስፋት ለማልማት መቻላቸውን ገልጸዋል። አሁንም ዋና ትኩረታቸው ሰብሉን ከተባይ መጠበቅና ምርቱን ከብክነት በጸዳ መልኩ ሰብስቦ ለገበያ ማቅረብ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ ባለፈው የምርት ዘመን ከ163 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰሊጥ ሰብል ለምቶ ከ900 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
በሰሜን ሸዋ ዞን 543 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በመኸር እርሻ ለማልማት ተችሏል
Aug 16, 2026 181
ደብረ ብርሃን፤ ነሃሴ 10/2018(ኢዜአ)፡- በሰሜን ሸዋ ዞን በመኸር እርሻ 543 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በማልማት የእንክብካቤ ስራ እየተካሄደ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ ተውልኝ ሽባባው ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክረምቱ ወቅት በአጠቃላይ 563 ሺህ 043 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል።   እስካሁን በተደረገ ጥረትም 542 ሺህ 960 ሄክታር መሬት በዘር መሸፈን ተችሏል። ከ332 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የተካሄደው የዘር ስራ ከእቅዱ ጋር ሲነጻጸር ከ96 በመቶ በላይ መሳካቱን ተናግረዋል። በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥም 288 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በጤፍ፣ ስንዴ፣ ባቄላና ማሾ ሰብሎች በኩታ ገጠም የአሰራር ዘዴ የለማ መሆኑን ባለሙያው አረጋግጠዋል። ዝናብ ዘግይቶ ቢጥልም፣ በግብርና ባለሙያዎች የተጠናከረ ድጋፍ አርሶ አደሩ ሌት ተቀን እንዲረባረብ በማድረግ የተሻለ አፈፃፀም ማስመዝገብ ተችሏል ብለዋል። ምርታማነትን ለማሳደግም 720 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ እና 109 ሺህ 222 ኩንታል ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ ማዋል መቻሉን አቶ ተውልኝ አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅትም የለማውን ሰብል በማረም፣ተባይን በመከላከልና በመንከባከብ ተግባር ላይ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በዞኑ የሞረትና ጅሩ ወረዳ የገርባ ቀበሌ አርሶ አደር መዝገቡ ወልዴ በበኩላቸው፣ ሰባት ነጥብ አምስት ሄክታር መሬታቸውን በኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴ በመጠቀም በስንዴና አተር ሰብል መሸፈናቸውን ተናግረዋል።   ምርታማነትን ለማሳደግ ማዳበሪያ፣ ምርጥ ዘርና ሌሎች ቴክኖሎጅዎችን ከመጠቀም ባሻገር፣ የአረምና የተባይ መከላከል ስራ እያካሄዱ መሆኑንም ገልጸዋል። በዞኑ የመርሐቤቴ ወረዳ ሰባጌ ሀሮ ገንዳ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት ቄስ አውግቸው ማሞ በበኩላቸው፣ መሬታቸውን በኩታ ገጠም አሰራር ተጠቅመው በጤፍ፣ ማሽላና ባቄላ ሰብል መሸፈናቸውን አስታውቀዋል። ከዞኑ ግብርና መምሪያ የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፣ በዞኑ ከ2018/19 የመኸር ምርት ዘመን 20 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማምረት ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም