ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በይርጋዓለም ከተማ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የዶሮ አርቢዎችን ኢኮኖሚያዊ አቅምን እያሳደገ ነው
Aug 19, 2026 137
ይርጋለም፤ ነሀሴ 13/2018 (ኢዜአ)፡-በይርጋዓለም ከተማ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዶሮ እርባታ ሥራ የተሰማሩ ማህበራት ከእንቁላል ምርታቸው ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን ገለጹ። በሲዳማ ክልል ማዕከላዊ ሲዳማ ዞን ይርጋዓለም ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው ማህበራት እንደገለጹት፣ የተሰማሩበት የዶሮ እርባታ ሥራ የእንቁላል ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የኢኮኖሚ አቅማቸውን እያሳደገው ነው። ከእንቁላል ሽያጭ በሚያገኙት ገቢ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱንም ለኢዜአ ገልጸዋል።   ‎በከተማው የጌዶሴይ ዶሮ እርባታ ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ከተማ ካቢሶ ሥራውን በ1 ሺህ የእንቁላል ጣይ ዶሮዎች እንደጀመሩ አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ያሏቸው የዶሮዎች ቁጥር 4 ሺህ መድረሱን ተናግረዋል። ከእነዚህም በቀን ከ3 ሺህ 700 በላይ እንቁላል እንደሚሰበስቡና ከሽያጩም የተሻለ ገቢ እያገኙ መሆናችውን አስረድተዋል።   ከእንቁላል ምርት ባለፈ የአንድ ቀን ጫጩቶችን በማስመጣትና አሳድገው በ48 ቀናቸው ለተጠቃሚዎች በማስረከብ ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በሥራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ከመንግስት የመስሪያ ቦታ፣ የስልጠናና ሌሎች ድጋፎችን እያገኙ ማግኘታቸውን ተናግረዋል።   የደረሰና ቤተሰቡ የዶሮ እርባታ ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ደረሰ አሰፋ በበኩላቸው "የዶሮ እርባታ ሥራ አስፈላጊ መኖና ሕክምናን ከማሟላት ባለፈ በጥንቃቄ መስራት ከተቻለ ትርፋማ ያደርጋል" ብለዋል። በአንድ ሺህ የእንቁላል ጣይ ዶሮዎች የጀመሩትን ሥራ አስፋፍተው በአሁኑ ወቅት ከ10ሺህ በላይ ዶሮዎች እንዳሏቸው ገልፀዋል፡፡ በቀን ከ9 ሺህ በላይ እንቁላል ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ደረሰ፣ በስራቸው ለሌሎቸም የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ነው የተናገሩት ከመንግስት ነጻ የዶሮ ክትባቶችን ጨምሮ የሙያና የተለያየ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑንም ገልፀዋል፡፡   የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ምክትልና የዝርያ ማሻሻልና መኖ ልማት ዘርፍ ኃላፊ አደገ አለሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው በክልሉ በሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር ከተከናወኑ ተግባራት መካከል የዶሮ ልማት ሥራ ትልቅ እመርታ ማሳየቱን ገልጸዋል፡፡ የዶሮ ሀብት ልማት በየቤታቸው የተወሰኑ ዶሮዎችን የሚያረቡ አርሶ አደሮች፣ በማህበር ተደራጅተው የሚሰሩ ዜጎችን እንዲሁም በግል የሚያለሙ ባለሀብቶችን ተጠቃሚ አድርጓል ብለዋል። በዘርፉ ለተሰማሩ ማህበራት እና ዶሮ ፈላጊዎች የዶሮ አቅርቦት፣ የሙያ እገዛና ሌሎች የድጋፍና ክትትል ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ኃላፊው አደገ (ዶ/ር) ጠቁመዋል፡፡ እንደእሳቸው ገለጻ ከአምስት ዓመት በፊት በክልሉ በዓመት ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን በታች የነበረውን የዶሮ ሥርጭት በአሁኑ ወቅት 20 ሚሊዮን ለማድረስ ተችሏል። በተያዘው 2019 በጀት ዓመትም 24 ሚሊዮን ዶሮዎችን ለማሰራጨት ማታቀዱን ጠቁመዋል፡፡    
በድሬደዋ በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተሰማሩ አልሚዎችን በመደገፍ የኮንፍረንስ ቱሪዝምን ማሳደግ ተችሏል
Aug 19, 2026 77
ድሬደዋ፤ ነሐሴ 13/2018(ኢዜአ)፦ በድሬደዋ ከተማ አስተዳደር በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተሰማሩ አልሚዎችን በመደገፍ የኮንፍረንስ ቱሪዝምን ማሳደግ መቻሉን የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ አመራር አካላት በሆቴል ኢንቨስትመንት ለመሰማራት ፈቃድ ወስደው ግንባታ ላይ የሚገኙ ባለኮከብ ሆቴሎችን የመስክ ጉብኝት አድርገዋል። ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ አስተዳደሩ የከተማዋን ኢንቨስትመንት ለማስፋፋት የቀየሰው የአሰራርና የህግ ማእቀፍ በርካታ አልሚዎችን ወደ ስራ ማስገባት አስችሏል። ለዚህም የመሠረተ ልማት፣ የመሬት አቅርቦት፣ የውሃ፣ የኤሌክትሪክ፣ የፋይናንስ እና ሌሎች ድጋፎችን ከመስጠት አኳያ ከተቋማት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል። ይህም በተለይም በሆቴሎች ዘርፍ ፈቃድ ወስደው በግንባታ ላይ የነበሩ አልሚዎች ስራቸውን አጠናቀው ወደ አገልግሎት በመግባት የቱሪዝሙን እንቅስቃሴ እያሳደጉ መሆናቸውን አስረድተዋል። ለአብነትም በበጀት አመቱ በግንባታ ላይ የነበሩ አምስት ሆቴሎች ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን አንስተዋል። ይህም ከተማዋን የቱሪዝም ኮንፍረንሰ ማእከል ለማድረግ የተጀመረውን ጥረት ለማሳካትና የቱሪስቶችን ቆይታ ለማራዘም ማገዙን ገልጸዋል ። የዛሬው ጉብኝትም አስተዳደሩ በሆቴል አገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩ ባለሃብቶችን ለማበረታታት ያለመ ነው ብለዋል። እንዲሁም በግንባታ ላይ ያሉ ሆቴሎችን በማበረታታት በፍጥነትና በጥራት ወደ አገልግሎት ለማስገባት አቅጣጫ ለማስቀመጥ መሆኑን ጠቅሰዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወንደሰን አባይ አስተዳደሩ ተፈጥሮአዊና ታሪካዊ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማት የዘርፉን ጠቀሜታ ለማጉላት እየሰራ ነው ብለዋል። በዚህም መስህቦቹን ለጎብኚዎች አመቺ የማድረግና ከከተማዋ ኮሪደር ልማት ጋር ተሰናስሎ እንዲሄድ መደረጉን ገልጸዋል። በከተማዋ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶችን ፍሰትና የቆይታ ጊዜ ለማራዘም የቱሪስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ማስፋፋት ላይ ትኩረት መሰጠቱን ጠቁመዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት አመት ከ700 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥ እና ከ15 ሺህ በላይ ቱሪስቶች መስህቦቹን መጎብኘታቸውን አስረድተዋል። የከተማዋ የቱሪዝም ልማትም የስራ እድልን ለማስፋትና የከተማውን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ከፍ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል። በተያዘው በጀት አመትም በቱሪዝም ዘርፍ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በግንባታ ላይ ከሚገኙ ባለኮኮብ ሆቴሎች ባለቤት አቶ ሱራፌል ሲሳይ በበኩላቸው የከተማ አስተዳደሩ ለዘርፉ የሚያደርገው ድጋፍና ክትትል ስራቸውን ለማቀላጠፍ እያገዛቸው መሆኑን ጠቅሰዋል። በግባታ ላይ የሚገኘው ሆቴልም ለከተማዋ የቱሪስት ፍሰትና ለወጣቶች የስራ ዕድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል።      
በአማራ ክልል የአፈር ለምነትን የሚያሻሽል የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል
Aug 19, 2026 89
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል በበጀት ዓመቱ የአፈር ለምነትን የሚያሻሽል 86 ሚሊዮን ሜትር ኩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደተግባር መገባቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የአፈር ለምነት ባለሙያ አቶ አምሳሉ አድማስ ለኢዜአ እንደገለጹት በአሲድ የተጠቃ አፈር ለምነትን ለመመለስና የሰብል ምርታማትን ለማሳደግ የተፈጥሮ ማዳበሪያን አዘጋጅቶ መጠቀም ጠቀሜታው የጎላ ነው።   ለዚህም በበጀት ዓመቱ ከ3 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚበልጡ አርሶ አደሮችን በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅት በማሳተፍ 86 ሚሊዮን ሜትር ኩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ግብ ተይዞ ወደተግባር ተገብቷል። ከቅጠላቅጠሎች፣ ከተረፈ ምርት፣ ከከብቶች እዳሪ፣ ከአመድና ለኮምፖስት ዝግጅት ጠቃሚ ከሆኑ ሌሎች ንጥረ ነገሮች ጥራቱን ጠብቆ እንዲዘጋጅ ለአርሶ አደሩ ሙያዊ ድጋፍ እየተሰጠ መሆኑንም ገልጸዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያ ሳይንሳዊ ሂደቱን ጠብቆ ከተዘጋጀ የአፈር ቅንጣትና ለምነት እንዲሻሻል፣ የሰብል ምርታማነት እንዲጨምር፣ አፈር በውስጡ ውሃን ለረጅም ጊዜ እንዲቋጥር የጎላ ጠቀሜታው እንዳለውም አመልክተዋል። በበጀት ዓመቱ የሚዘጋጀው የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለቀጣይ ዓመት መስኖና የመኽር እርሻ ጥቅም ላይ ለማዋል ከወዲሁ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በማዳበሪያ ዝግጅቱ እየተሳተፉ ካሉት መካከል በምዕራብ ጎጃም ዞን ቡሬ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ታደሰ አለሙ በሰጡት አስተያየት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማዘጋጀትና መጠቀም ከጀመሩ ከ15 ዓመት በላይ እንደሆናቸው ገልጸዋል። በተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘገጃጀት ላይ ከግብርና ባለሙያዎች ባገኙት የካበተ ልምድና ዕውቀት በዓመት እስከ 23 ሜትር ኩብ ኮምፖስት ማዳበሪያ በጥራት አዘጋጅተው እንደሚጠቀሙ ተናግረዋል። የሚያዘጋጁትን ኮምፖስት ማሳቸው ላይ በመጨመር የአፈር ለምነትን ከማሻሻል ባለፈ የሰብል ምርታማነትና ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን አመልክተዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘጋጅተው መጠቀም ከጀመሩ ወዲህ ለምነቱን አጥቶ ከምርት ውጭ ሆኖ የቆየ ግማሽ ሄክታር መሬት ለምነቱ መመለሱን የገለጹት ደግሞ በዞኑ የሰከላ ወረዳ አርሶ አደር ፈጠነ አስረስ ናቸው። ከዚህም በየዓመቱ እስከ 12 ኩንታል የስንዴና የገብስ ምርት በመሰብሰብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው፣ በተያዘው በጀት ዓመትም 18 ሜትር ኩብ ኮምፖስት በጥራት አዘጋጅተው ለመጠቀም ወደሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። የቢሮው መረጃ እንደሚያመለክተው በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተዘጋጀ ከ81 ሚሊዮን ሜትር ኩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለመስኖና ለመኸር ሰብል ልማት ጥቅም ላይ መዋሉ ታውቋል።  
በዞኖች ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Aug 19, 2026 92
ሆሳዕና ፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተከናወነ ያለው ተግባር ውጤታማ መሆኑን የጉራጌ፣ ስልጤና ከምባታ ዞኖች አስታወቁ። በስልጤ ዞን ግብርና መምሪያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከድር ሁሴን እንዳሉት፣ በዞኑ የማህበረሰቡን ተሳትፎ በማሳደግ ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተደረገ ባለው ጥረት ውጤት ተመዝግቧል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በራስ አቅም ሰብዓዊ ድጋፍን ለመሸፈን የሚውል የእህል ክምችት ለመያዝ በተከናወነ ተግባር፣ እስከ አሁን ከ11 ሺሕ 860 ኩንታል በላይ ምርት በወል መሬት ላይ አምርቶ ማከማቸት እንደተቻለ ገልጸዋል። በተጨማሪም ማህበረሰቡን በማሳተፍ 22 ሚሊዮን ብር በጥሬ ገንዘብና የተለያዩ ቁሳቁሶችን በማሰባሰብ ማከማቸት ተችሏል ብለዋል። በተያዘው የበጀት ዓመትም በዞኑ በመኸር ወቅት 207 ሄክታር ማሳ በበቆሎ ሰብል ለዚሁ ተግባር እየለማ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በተጨማሪም 30 ሚሊዮን ብር በማሰባሰብ ለሚከሰቱ ሰው ሰራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   በጉራጌ ዞን ግብርና መምሪያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጊዜወርቅ አለሙ በበኩላቸው፣ ለተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት በማህበረሰብ ተሳትፎ 6 ሺሕ 800 ኩንታል እህል ማከማቸት ተችሏል ብለዋል። በተያዘው የበጀት ዓመትም በዞኑ በመኸር ወቅት 260 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች የለማ ሲሆን ፣ ከ19 ሚሊዮን ብር በላይ የመጠባበቂያ ገንዘብ ለማሰባሰብ ግብ ተጥሎ ወደ ትግበራ መገባቱን አመልክተዋል።   በከምባታ ዞን ግብርና መምሪያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አስራት ማቲዎስ እንደገለጹት ደግሞ፣ በዞኑ በተለያዩ ምክንያቶች ለሚከሰቱ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ መስጠት እንዲቻል ከማህበረሰቡ ጋር ስምምነት ላይ ተደርሷል። በዚህም 480 ኩንታል የምግብ እህል ከማምረት ባሻገር፣ 22 ሚሊዮን ብር በጥሬ ገንዘብ መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። በመኸር እርሻም 180 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች እየለማ ሲሆን 124 ሚሊዮን ብር ለማሰባሰብ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ጠቁመዋል።    
ኢትዮጵያ ምርቶቿን በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ በማድረግ የወጪ ንግድ አቅሟን እያሳደገች ነው
Aug 19, 2026 194
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ምርቶቿን በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ በማድረግ የወጪ ንግድ አቅሟን እያሳደገች መሆኑን የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር በኢትዮጵያ ከሚገኘው የቻይና ኤምባሲ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የኢትዮጵያና የቻይናን ዘላቂና ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ወደ ላቀ የንግድና ኢኮኖሚ ትስስር የሚያሸጋግረውና የፕሮሞሽን ሥራዎች አካል የሆነ "Export to China" መድረክ በይፋ ተጀምሯል።   በመድረኩ የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፣ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ፣ የሁለቱ ሀገራት ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ አስመጪና ላኪዎች ታድመዋል። በመድረኩ የቻይና አስመጪዎች ጥራት ያላቸውን የኢትዮጵያ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በስፋት እንዲገዙ ለማድረግ የሚያስችል የፕሮሞሽን ሥራዎች ተከናውኗል። በዚህም ከ340 ሚሊዮን ዶላር በላይ ዋጋ ያላቸው 33 የንግድ ለንግድ (B2B) የግብይት ኮንትራቶች በቡና፣ ሰሊጥ፣ አኩሪ አተር፣ በጨርቃጨርቅ እና በማዕድን ዘርፎች ወደ ውጭ ለመላክ ተፈራርመዋል። የንግድ እና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት የስምምነቱ ዓላማ የኢትዮጵያን የወጪ ንግድ ገቢ ግኝት ለማሳደግ የሚያስችል የፕሮሞሽን ሥራዎችን በቻይና ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። ሚኒስቴሩ ከቻይና ኤምባሲ ጋር ሰፋፊ ውይይቶችን ሲያደርግ መቆየቱን ገልጸው፤ ስምምነቱ ከብዙ ሥራዎች በኋላ የተገኘ ውጤት መሆኑንም ገልጸዋል። 33 የሚጠጉ ስምምነቶች መፈረማቸውን ገልጸው፤ እነኝህም 340 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ሊያስገኙ የሚችሉ መሆኑን ጠቁመዋል። ስምምነቱን ወደ ትልቁ የቻይና ገበያ ለመግባት በቻይና መንግሥት የተቀረጸው ኢኒሼቲቭ አካል መሆኑን አንስተዋል። በቡና፣ በቅባት እህል፣ በጥራጥሬ፣ በቆዳ፣ በማዕድን ምርቶች እና በጨርቃ ጨርቅ ላይ ከስምምነት መደረሱን ተናግረዋል። ስምምነቱ ከቃል በዘለለ ተግባራዊ ውጤት የተገኘበት ስኬት መሆኑንም ገልጸዋል። መንግሥት በ2019 በጀት ዓመት ከወጪ ንግድ 13 ነጥብ 4 ቢሊዮን ዶላር ለማግኘት ማቀዱን ገልጸው፤ ስምምነቱ ይህንን ማሳካት የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። እንዲሁም የኢትዮጵያ ምርቶች በዓለም ገበያ የሚያስተዋውቅና ተወዳዳሪነታቸውን በማሳደግ የተያዘውን ውጥን የሚያሳካ መሆኑን አመላክተዋል። በቀጣዮቹ ጊዜያትም ከተለያዩ ሀገራት ጋር ምርቶችን በጥራት በዋጋ እና በብዛት ተወዳዳሪ ሆነው እንዲቀርቡ በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን ምርቶች በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ ማድረግ የሚያስችሉ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጠሉም እንዲሁ።   በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ በበኩላቸው የስምምነቱ ዓላማ ለሁሉም የወጪ ንግድ ትልቅ ገበያ ማግኘት መሆኑን ገልጸዋል። ቻይና በከፍተኛ ፍጥነት በማደግ ላይ እንደምትገኝ ገልጸው፤ የኢትዮጵያ እጅግ አያሌ ምርቶችና የበለጸጉ ተፈጥሯዊ ሀብቶችም እንዲሁ በፍጥነት በማደግ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በሁለቱ ገበያዎች እና ምርቶች መካከል ያለው ትስስር የሀገራቱን እድገት ለማፋጠን አስፈላጊ መሆናቸውንም አመላክተዋል። ስምምነቱ ቻይና ከአፍሪካ እና ከኢትዮጵያ ጋር የዜሮ ታሪፍ ፖሊሲ ከተቀበለች እና መተግበር ከጀመረች ወዲህ የተወሰደ ወሳኝ እርምጃ መሆኑን ጠቁመዋል።
በአማራ ክልል ኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን የመኸር እርሻ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል- መምሪያው
Aug 19, 2026 84
ደሴ፤ነሐሴ 13/2018( ኢዜአ):-በአማራ ክልል ኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን በመኸር ወቅት የሚከናወነው የአረምና ተባይ ቁጥጥር ሥራን በማጠናከር ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ደጀኔ ከበደ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በያዝነው መኸር በኩታ ገጠምና በመስመር በመዝራት እንዲሁም ግብአትን በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ይገኛል። በዚህም በ58 ሺህ 632 ሄክታር መሬት ላይ የተዘራውን የሰብል ቡቃያ የአረምና የተባይ ቁጥጥር ሥራ እየተካሄደ መሆኑን አስረድተዋል። የተዘራውን ሰብል እስከ ሁለት ጊዜ በማረም ነጻ የማድረግና በየቀኑ ማሳውን በማሰስ ተባይን በመቆጣጠር ምርታማነቱን ለማሳደግ እየተሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ይህም የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያና ኢንዱስትሪ ግብአት ለማቅረብ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም አልፎ አልፎ የሚስተዋለውን የዝናብ መቆራረጥ ለመቋቋም አርሶ አደሩ በማሳው ዳርና ዳር ጉድጓዶችን በመቆፈር ውሃ የማሰባሰብ ስራ እንዲያከናውን ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ነው ብለዋል። በአርጠማ ፉርሲ ወረዳ የዲምቱ ጨቆርሶ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መሀመድ ከድር በሰጡት አስተያየት፣ በዘንድሮው መኸር ሁለት ሄክታር ማሳቸውን በማሽላ፣ ማሾና በሌሎችም ሰብሎች አልምተዋል። ሰብሉን ከአረም በማጽዳትና በየቀኑ የተባይ ቁጥጥርና አሰሳ በማካሔድ ከ40 ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ አልመው እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል። ሌላው የዳዋጨፋ ወረዳ የሸክላ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሰይድ አደም በበኩላቸው፣ በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ በመታገዝ ፈጥነው የሚደርሱና ምርታማ የሆኑ ሰብሎችን ማልማት መቻላቸውን ገልጸዋል። አንድ ሄክታር መሬታቸውን ማሽላና ጤፍ በኩታ ገጠም ማልማታቸውን ጠቁመው፣ የዝናብ መቆራረጡን ለመቋቋም ውሃ እያሰባሰቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በብሔረሰብ አስተዳደር ዞኑ በመኸር ከለማው መሬት ከአንድ ነጥብ ስድስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
ግብፅ ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ያላትን ተፈጥሯዊ መብት ልታከብር ይገባል - የጂኦፖለቲክስ ባለሙያ ኤልያስ ዐቢይ
Aug 19, 2026 143
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ግብፅ የአባይ ወንዝን "ለብቻዬ ልጠቀም" የሚል ጊዜው ያለፈበት እሳቤ በመተው፣ የናይል ወንዝ የ86 በመቶ የውሃ ድርሻ ያላትን ኢትዮጵያ ተፈጥሯዊ የመልማት መብት ዕውቅና ልትሰጥ እንደሚገባ የጂኦፖለቲክስ ባለሙያው ኤልያስ ዐቢይ ገለጹ። የጂኦፖለቲክስ ባለሙያውና ደራሲው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ 135 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን የዕለታዊ ሕይወታቸውና ሀገራዊ የልማት ህልውናቸው እነዚህን ወሳኝ የተፈጥሮ ሀብቶች መሠረት ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ግብፅ ኢትዮጵያ የውሃ ሀብቷን እንዳትጠቀም ለማድረግ የምታደርገው ተደጋጋሚ ጥረት መልክአ-ምድራዊ እውነታንና የፍትሐዊ የውሃ አጠቃቀም መርሆዎችን ያላገናዘበ መሆኑንም አብራርተዋል።   ግብፅ ለፍትሐዊ የውሃ ሀብት አጠቃቀም መርሆዎች ተገዢ አለመሆኗን ጠቅሰው፤ ይህም የሚመነጨው የዓባይን ወንዝ በብቸኝነት "የእኔ ብቻ ነው" ከሚል ጊዜው ያለፈበትና ዘመኑን የማይመጥን እሳቤ እንደሆነ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በዓባይ፣ በባሮ-አኮቦ እና በተከዜ ተፋሰሶች አማካኝነት ከፍተኛ ድርሻ ቢኖራትም፤ ግብፅ ግን የቀጣናውን የጂኦፖለቲክስ ውጥረቶችና ዓለም አቀፍ ተፅዕኖዎችን መሣሪያ በማድረግ የኢትዮጵያን የልማት እንቅስቃሴዎችና የሃይድሮ-ኤሌክትሪክ ልማት ፕሮጀክቶችን ስታደናቅፍ ቆይታለች። እንደ ባለሙያው ገለጻ፣ ይህ ዓይነቱ የማደናቀፍ አካሄድ ከኢትዮጵያ የውሃ መሠረተ ልማት የሚገኘውን ግልጽ አካባቢያዊና ቴክኒካዊ ጥቅሞች ለረጅም ጊዜ ችላ ያለ ነው። ውሃ በኢትዮጵያ ቀዝቃዛና ጥልቅ ሸለቆዎች ውስጥ በመከማቸቱ በሰሃራ በረሃ በሚገኘው የናስር ሀይቅ ላይ በከፍተኛ ሙቀት ምክንያት የሚፈጠረውን ከፍተኛ የውሃ ትነትና መባከን እንደሚያስቀር ተናግረዋል። ከአስዋን ግድብ በስተጀርባ የሚገኘው የናስር ሀይቅ በዓለማችን እጅግ ሞቃታማ ከሆኑ አካባቢዎች አንዱ በሆነው በሰሃራ በረሃ ውስጥ ወደ 6,000 ካሬ ኪሎ ሜትር የሚጠጋ ቦታ እንደሚሸፍን አመልክተዋል። በከፍተኛ ሙቀት ምክንያት በዓመት ከ10 እስከ 15 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውኃ እንደሚባክንና ይህም ሙሉ በሙሉ የባሮ-አኮቦ ወንዝ ወደ ነጭ ዓባይ ከሚወስደው የውሃ መጠን ጋር እኩል መሆኑን ያስረዱት።   ከዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ጋር በተያያዘ የጨመረው የሙቀት መጠን ይህ የውሃ መባከን የበለጠ እንዲባባስ ማድረጉን ጠቅሰው፤ በዚህ ረገድም ኢትዮጵያ የውሃ ብክነትና ትነትን ከመቀነስ አንጻር ያላትን ሚና አጉልተው አሳይተዋል። የሀገሪቱን የወደፊት ስትራቴጂካዊ ጉዞ አስመልክቶ ኤልያስ እንደገለጹት፤ የውስጥ ጥንካሬ፣ ፈጣን ኢኮኖሚያዊ እድገትና ሀገራዊ አንድነት ለውጭ ጫናዎችና ተቃውሞዎች ኢትዮጵያ የምትሰጠው ዋናና ውጤታማ ምላሾች ናቸው። ሁሉን አቀፍ ልማትን ማፋጠን እና ሀገራዊ ውይይትን ማጎልበት ዘላቂ ሀገራዊ ግቦችን ለማሳካት ወሳኝ መሆኑንም አክለው ገልጸዋል። ይህም በበለጸገች ኢትዮጵያ አማካኝነት በአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ውስጥ ሰፊ የኢኮኖሚ ትስስርና ሰላም እንዲሰፍን አስተማማኝ መሠረት ይጥላል ብለዋል።
ከውጭ የሚገባውን የጥጥ ምርት በሀገር ውስጥ ለመተካት በተከናወኑ ተግባራት ውጤት እየተመዘገበ ነው
Aug 19, 2026 119
ጂንካ፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ከውጭ የሚገባውን የጥጥ ምርት በሀገር ውስጥ ለመተካት በተከናወኑ ተግባራት ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የጥጥ ምርት በስፋትና በጥራት ለማምረት የግል ባለሀብቱን ያሳተፈ ርብርብ እየተደረገ ይገኛል። በክልሉ ደቡብ ኦሞ ዞን በጥጥ ልማት ዘርፍ የተሰማሩ ባለሀብቶችን የስራ እንቅስቃሴን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ጎብኝተዋል። የቢሮ ኃላፊው በወቅቱ እንዳሉት፤ ከውጭ የሚገባውን የጥጥ ምርት በሀገር ውስጥ ለመተካት የተጀመረው ጥረት አበረታች ለውጥ እያመጣ ይገኛል። በክልሉ ጥጥን ጨምሮ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ የግብርና ምርቶችን ለማልማት የሚያስችል አቅም እንዳለም ተናግረዋል። የሀገር ውስጥ የጥጥ ምርትን ለማሳደግ የተጀመረውን ጥረት በማገዝ ረገድ የናሳ እርሻ ልማት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ልማታዊ ባለሀብቶችን በማበረታታት የሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት መሪ ተዋናይ እንዲሆኑ የክልሉ መንግስት የማያቋርጥ ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል። የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ በበኩላቸው፤ የደቡብ ኦሞ ዞን ለጥጥ እርሻ ልማት ተስማሚ የሆነ ስነ-ምህዳር ያለው በመሆኑ የግል ኢንቨስትመንቶች በጥጥ እርሻ ልማት ቢሰማሩ ውጤታማ እንደሚሆኑ ተናግረዋል። በጥጥ ልማት በመሳተፍ ላይ ከሚገኙ ኢንቨስተሮች የናሳ ብራይሌ እርሻ ልማት ለአካባቢው አርብቶ አደሮች ከሚፈጥረው የስራ ዕድል ባሻገር የቴክኖሎጂ ሽግግር በማድረግ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ዞኑ በዘርፉ መሰማራት ለሚፈልጉ ባለሀብቶች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም የመምሪያ ኃላፊው ጠቁመዋል። የናሳ ብራይሌ እርሻ ልማት በደቡብ ኦሞ ዞን በባና ፀማይ ወረዳ የወይጦ ወንዝን በመጥለፍ ከ2 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ጥጥ እያመረተ እንደሚገኝ የተናገሩት የእርሻ ልማቱ ስራ አስኪያጅ አቶ አረጋዊ ገብረስላሴ ናቸው። ድርጅቱ በዋናነት የሀገሪቱን የጥጥ ምርት ፍላጎት ሙሉ ለሙሉ ለመተካት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የእርሻ ልማቱ ለሀገር ውስጥ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች ጥሬ ዕቃ ከማቅረብ ባለፈ፣ በአካባቢው ባስገነባው የጥጥ መዳመጫ ፋብሪካ እሴት በመጨመር ወደ ውጭ ሀገራት በመላክ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እያስገኘ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በተጨማሪም ለ300 ቋሚ እና 3 ሺህ ለሚደርሱ የአካባቢው ነዋሪዎች ጊዜያዊ የስራ እድል መፍጠሩን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያዊያን በርካታ ግድቦችን የመገንባት አቅሙም ዝግጁነቱም አላቸው-አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር)
Aug 19, 2026 196
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያዊያን በርካታ ግድቦችን የመገንባት አቅሙም ዝግጁነቱም እንዳላቸው የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር) ተናገሩ። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት በዋናነት የግድቡን ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ በማስተባበር ግንባታው በስኬት እንዲጠናቀቅ ያደረገ ተቋም ነው። የጽሕፈት ቤቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አረጋዊ በርሄ (ዶ/ር)፤ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የዓባይ ውሃ ፍትሃዊ አጠቃቀም ላይ ለዘመናት የቆየ የተዛባ አረዳድን የቀየረ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። ግድቡ የትኛውንም ሀገር እንደማይጎዳና ይልቁንም ቀጣናውን በኢነርጂ እያስተሳሰረ መሆኑ በተግባር መረጋገጡን ጠቅሰዋል። ነገር ግን ግብጽ ይህንን እውነታ በመካድ አሁን ላይ የቀደመ በጩኸት የማደናገር ተግባሯን በስፋት እያከናወነች መሆኑን ተናግረዋል። ዓባይ የተፋሰሱ ሀገራት በትብብር የሚጠቀሙት ሃብት እንጂ የግብጽ የግል ንብረት አይደለም ያሉት አረጋዊ (ዶ/ር)፤ከዚህ አኳያ የግብጽ የማደናገር ዘመቻ ሊቆም ይገባል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ ዋነኛ ዓላማ በትብብር ማደግ መሆኑንም አብራርተዋል። ኢትዮጵያዊያን በትብብር ምን ማሳካት እንደሚችሉ በታላቁ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ ማሳየታቸውን አንስተው፤ በቀጣይም በርካታ ግድብ የመገንባት አቅሙም ዝግጁነቱም አላቸው ብለዋል። በታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ወቅት ሕዝብን በማስተባበር ረገድ በርካታ ጠቃሚ ልምድ መገኘቱንም ተናግረዋል። ይህ ልምድ በቀጣይ ለሚከናወኑ መሰል የልማት ስራዎች ትልቅ ግብዓት መሆኑንም አብራርተዋል።
ኢትዮጵያ ከአህጉራዊ የልማት ዕቅዶች ጋር የተጣጣመ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ምርታማነት አቅም እየገነባች ነው
Aug 18, 2026 315
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከአህጉራዊ የልማት ዕቅዶች ጋር የተጣጣመ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ምርታማነት አቅም እየገነባች መሆኗን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። የምሥራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግሥታት (ኢጋድ) አባል ሀገራት የግብርና ትራንስፎርሜሽን አፈጻጸም ግምገማ እና ከ2026 እስከ 2035 የሚተገበረውን የካምፓላ ድንጋጌ ማዕቀፍ አስመልክቶ በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው የሁለት ቀናት መድረክ ተጠናቋል። የግብርና ሚኒስትር አማካሪ ዜና ሀብተወልድ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል። ሀገሪቱ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ በሌማት ትሩፋት፣ በመስኖ ስንዴ እና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ላይ ትኩረት በመስጠት ስኬታማ መሆኗን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ደረጃ በአጀንዳ 2063 የተቀመጠውን የበለጸገች አፍሪካን የመፍጠር ርዕይ ለማሳካት የሚያስችሉ ሥራዎችን በቁርጠኝነት እያከናወነች ትገኛለች ብለዋል። በመሆኑም አህጉራዊ አቅጣጫዎችን ከሀገራዊ እቅዶች ጋር በማጣጣም የግብርናውን ዘርፍ ይበልጥ ለማሳደግ እና የላቀ ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል። ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እና ምርታማነትን ለማሳደግ በሌማት ትሩፋት፣ በበጋ መስኖ ስንዴና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ላይ ትኩረት በመስጠት ስኬታማ ተግባራትን ማከናወኗን አስረድተዋል። በምሥራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግሥታት (ኢጋድ) የፖሊሲና የምግብ ዋስትና ኤክስፐርት ሲልቪያ ሄንጋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን ለአርሶ አደሩ ማዳረስና አቅሙን መገንባት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ሀገራዊ እና ቀጣናዊ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እሴት መጨመር፣ በድህረ-ምርት አስተዳደር እንዲሁም አህጉር አቀፍ የንግድ ትስስርን ማጠናከር ላይ ልዩ ትኩረት ሊደረግ እንደሚገባ ገልጸዋል። በተጨማሪም ሕፃናት እና እናቶች የተመጣጠነ ምግብና አስፈላጊ ንጥረ ነገሮችን እንዲያገኙ መሥራት ወሳኝ መሆኑን አንስተው፣ አባል ሀገራት የግብርና ሥርዓቱን ለማሻሻል በቁርጠኝነት ሊሠሩ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።  
የቤቶች ልማት ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ አካታች አካሄድ ተግባራዊ እየተደረገ ነው
Aug 18, 2026 285
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የቤት ልማት ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ አካታች አካሄድ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ። የውጭ ዜጎች በኢትዮጵያ የመኖሪያ ቤት ባለቤት መሆን የሚችሉበት አዋጅ ቁጥር 1388/2017 ቀደም ሲል መጽደቁ ይታወሳል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር በአዋጁ መሠረት የተዘጋጀውን መመሪያ የማስተዋወቂያ መድረክ ከባለድርሻ አካላት ጋር የማስተዋወቅ ውይይት አካሂዷል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፣ ባለፉት ዓመታት በኢትዮጵያ የመኖሪያ ቤቶችን አቅርቦት ለማስፋት ከግሉ ዘርፍ ጋር በጋራ የቤት አቅርቦት አማራጮችን ለማስፋት እየተሠራ ነው። የውጭ ዜጎች በኢትዮጵያ የመኖሪያ ቤት ባለቤት እንዲሆኑ የሚያስችለው መመሪያ የቤት ልማት ኢንቨስትመንትን ለማሳደግና በሁሉም አካባቢዎች ተመጣጣኝ ዕድገትን ለማረጋገጥ ጉልህ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል። ሀገራት ተጨማሪ የካፒታል ኢንቨስትመንት ለማሳደግ የውጭ ዜጎችን የቤት ባለቤት ማድረግን እንደ አንድ መንገድ እንደሚጠቀሙ ጠቁመው፣ በኢትዮጵያም ኢኮኖሚውን ክፍት በማድረግ የውጭ ዜጎች የመኖሪያ ቤት ባለቤት የሚሆኑበትን አዋጅ መውጣቱን አንስተዋል። የቤት ልማት አቅርቦትን ማሳደግ፣ የቴክኖሎጂ ሽግግርን ማስፋት፣ የሥራ ዕድልን ማስፋትና የክልል ከተሞች ተመጣጣኝ ዕድገት እንዲያስመዘግቡ ማድረግ ከአዋጁ ጠቀሜታዎች መካከል እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። አዋጁን ለመተግበር የተዘጋጀውን መመሪያ መሠረት በማድረግ ሁሉም ተቋማት ተመሳሳይ ግንዛቤ እንዲጨብጡ ማድረግና ወደ ተቀናጀ እንቅስቃሴ መግባት ያስፈልጋል ብለዋል። በከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር የቤቶች ልማት መሪ ሥራ አስፈጻሚ ጸጋዬ ሞሼ ባቀረቡት ማብራሪያ መመሪያው ኢትዮጵያ ከሌሎች ሀገራት ተሞክሮ በመውሰድ የውጭ ዜጎች የመኖሪያ ቤት ባለቤት የሚሆኑበትን ሥርዓት ለመዘርጋትና ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ ያለመ ነው ብለዋል። በአዲስ አበባና ሸገር ከተሞች የውጭ ዜጎች የቤት ባለቤት ለመሆን ከሚያስፈልጉ ቅድመ ሁኔታዎች አንዱ ዝቅተኛው የግዥ ዋጋ 150 ሺህ ዶላር ሲሆን፣ በሌሎች ክልሎች ከተሞች ደግሞ ከ100 ሺህ እስከ 120 ሺህ ዶላር መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም ከወንጀል ነፃ ማረጋገጫ፤ የሰላምና ደኅንነት ማረጋገጫ ሰነዶች፣ ከኢንቨስትመንት ኮሚሽን የተሰጠ ሕጋዊ የኢንቨስትመንት ፈቃድና የጽሑፍ ማረጋገጫ፣ ፓስፖርትና ሌሎች አስፈላጊ ሰነዶችን ማሟላት እንደሚያስፈልግም አንስተዋል። በመመሪያው አተገባበር ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር በተደረገው ውይይት፣ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንትንና የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳደግ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተጠቅሷል። ሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውርን ለመግታትና ሕገ-ወጥ አሠራርን ለመከላከል የፋይናንስ ደኅንነትና ቁጥጥርን ለማጠናከር እንደሚሠራና የመመሪያ ጥሰት በሚፈጽሙ አካላት ላይ ጠንካራ ተጠያቂነት እንደሚኖር ተነስቷል።      
በዓለም የንግድ ድርጅት አባልነት ዙሪያ ከዩናይትድ ኪንግደም የድርድር ቡድን ጋር ውይይት እየተካሔደ ነው
Aug 18, 2026 346
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር ከዩናይትድ ኪንግደም የድርድር ቡድን ጋር የሚያካሂደው የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት የሁለትዮሽ የገበያ ዕድል ድርድር በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። በመክፈቻው ላይ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ(ዶ/ር) ፤ ከ23 ዓመታት በላይ የወሰደውን የኢትዮጵያን የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት ድርድር በ2026 መጨረሻ ለማጠናቀቅ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን ለዩናይትድ ኪንግደም የድርድር ኮሚቴ አባላት አብራርተዋል።   ሚኒስትሩ በንግግራቸው ኢትዮጵያ የልማት ፍላጎቷን ያገናዘበ ገንቢና መፍትሔ-ተኮር የገበያ ሁኔታ ማቅረቧን እና እስከ አሁን ከ11 ሀገራት ጋር ድርድር ማጠናቀቋን አረጋግጠዋል። የዩናይትድ ኪንግደም መንግሥት ለኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት ሂደት ለሚያደርገው ድጋፍና አጋርነት ምስጋናቸውን ማቅረባቸውን ከሚኒስቴሩ የተገኘው መረጃ ያመለክታል። ለሁለት ቀናት በሚቆየው ውይይት ስምምነቱን በይፋ ለመፈራረም የሚያስችል ውጤት እንደሚጠበቅም ተገልጿል።
ኢትዮጵያ በሌማት ትሩፋት፣ በመስኖ ስንዴ እና አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ስኬታማ ተግባራትን አከናውናለች
Aug 18, 2026 360
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እና ምርታማነትን ለማሳደግ በሌማት ትሩፋት፣ በመስኖ ስንዴ እና አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ትኩረት በመስጠት ስኬታማ ተግባራትን ማከናወኗን የግብርና ሚኒስቴር ገለፀ። የምስራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) አባል ሀገራት የግብርና ትራንስፎርሜሽን አፈጻጸም ግምገማ እና ከ2026 እስከ 2035 የሚተገበረውን የካምፓላ ድንጋጌ ማዕቀፍን አስመልክቶ በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው የሁለት ቀናት መድረክ ተጠናቋል።   የግብርና ሚኒስትር አማካሪ ዜና ሀብተወልድ እንዳሉት፣ በኢትዮጵያ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል። ሀገሪቱ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ በሌማት ትሩፋት፣ በመስኖ ስንዴ እና አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ላይ ትኩረት በመስጠት ስኬታማ መሆኗን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ደረጃ በአጀንዳ 2063 የተቀመጠውን የበለጸገች አፍሪካን የመፍጠር ርዕይ ለማሳካት የሚያስችሉ ሥራዎችን በቁርጠኝነት እያከናወነች ትገኛለች ብለዋል።   በመሆኑም አህጉራዊ አቅጣጫዎችን ከሀገራዊ እቅዶች ጋር በማጣጣም የግብርናውን ዘርፍ ይበልጥ ለማሳደግ እና የላቀ ውጤት ለማስመዝገብ በትኩረት እንደሚሠራ ተናግረዋል። በምሥራቅ አፍሪካ ልማት በይነ-መንግሥታት (ኢጋድ) የፖሊሲና የምግብ ዋስትና ኤክስፐርት ሲልቪያ ሄንጋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የሚያስችሉ ቴክኖሎጂዎችን ለአርሶ አደሩ ማዳረስና አቅሙን መገንባት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ሀገራዊ እና ቀጣናዊ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እሴት መጨመር እና በድህረ-ምርት አስተዳደር እንዲሁም አህጉር አቀፍ የንግድ ትስስርን ማጠናከር ላይ ልዩ ትኩረት ሊደረግ እንደሚገባ ገልጸዋል። በተጨማሪም ሕፃናት እና እናቶች የተመጣጠነ ምግብና አስፈላጊ ንጥረ ነገሮችን እንዲያገኙ መሥራት ወሳኝ መሆኑን አንስተው፣ አባል ሀገራት የግብርና ሥርዓቱን ለማሻሻል በቁርጠኝነት ሊሠሩ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።
የሚዛን አማን ከተማ የመልሶ ማልማት ሥራ ከተማዋን ለኑሮ ምቹና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት ነው
Aug 18, 2026 120
ሚዛን አማን፣ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፡-የሚዛን አማን ከተማ የመልሶ ማልማት ሥራ ከተማዋን ለኑሮ ምቹና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ እያደረጋት መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ገለጸ። የከተማዋ ከንቲባ ኢንጂነር ሰሎሞን ሌዊ ለኢዜአ እንደገለጹት ከተማዋን በተሻለ ደረጃ ለማሳደግ የመሠረተ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ ነው። ከተማ አስተዳደሩ የከተማዋን የመልሶ ማልማት ፕሮጀክት ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ መሆኑን ጠቁመው የከተማዋን እድገት የሚመጥኑ አገልግሎት ሰጪ ተቋማትና መሰረተ ልማቶች እንዲከናወኑ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡   በከተማዋ ለንግድ፣ ለሆቴልና ለቱሪዝም አገልግሎት የተገነቡ ደረጃቸውን የጠበቁ ሕንጻዎች የኢኮኖሚ እንቅስቃሴውን ከፍ እያደረጉ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዘርፉ እየመጣ ያለውን ለውጥ ለማጠናከር የኤሌክትሪክ አገልግሎት የኃይል ማሻሻያ፣ የውስጥ ለውስጥ መንገድና የውሃ አቅርቦት ትኩረት የተሰጣቸው ተግባራት መሆናቸውን አመልክተዋል። የመልሶ ማልማቱ ተግባር በኅብረተሰቡ ተሳትፎ ውጤታማ መሆኑን ገልጸው ከከተማ ኮሪደር ልማት ጋር ተሳስሮ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። የከተማ ልማት ኢንሼቲቮችን በከተማዋ በማስፋፋት ለነዋሪዎች ምቹና ጽዱ እንዲሁም ለኢንቨስትመንት ተመራጭ ከተማ ለማድረግ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል።   የሚዛን አማን አውሮፕላን ማረፊያና የደንቢ ኢኮ ሎጅ ፕሮጀክቶች አገልግሎት መጀመር የቱሪዝም እንቅስቃሴውን በማነቃቃት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያሳደጉ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል ። በመልሶ ማልማት ሥራ ለተለያዩ አገልግሎቶች ሕንጻ ከገነቡ የከተማዋ ባለሀብቶች መካከል አቶ ተረፈ ገርሲ ልማቱ ለከተማዋ ዕድገት ትልቅ ሚና ተጫውቷል ብለዋል።   ከተማዋ በተለይም ካለፉት አምስት ዓመታት ወዲህ ፈጣን እድገት እያሳች መሆኑን ገልጸዋል ። መምህር መላኩ ኬቃብ እና አቶ ስንታየሁ ዳሜ የተባሉ የከተማዋ ነዋሪዎች በበኩላቸው ከተማዋ ፈጣን ዕድገት ላይ መሆኗን የሚያረጋግጡ ተግባራት መሬት ላይ በተጨባጭ እየታዩ መሆኑን ተናግረዋል።   የመልሶ ማልማት ሥራው ከተማዋን በማስፋፋቱ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች መከፈታቸውን የጠቀሱት ነዋሪዎቹ ለዘላቂነቱ የድርሻቸውን ሚና ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።    
የኢትዮጵያ ታምርት አውደ ርዕዩ ተኪ ምርቶች ላይ የተሰማሩ ኢንዱስትሪዎችን የማነቃቃት ሚና ይኖረዋል
Aug 18, 2026 161
አሶሳ፤ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ታምርት አውደ ርዕይ ተኪ ምርቶች ላይ የተሰማሩ ኢንዱስትሪዎችን የማነቃቃት አበርክቶ እንደሚኖረው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ። ከነሐሴ 27 እስከ ጳጉሜን 1/2018 በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ከተማ ሀገር አቀፍ የኢትዮጵያ ታምርት አውደ ርዕይ ይካሄዳል። አውደ ርዕዩን አስመልከቶ መግለጫ የሰጡት የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ አመንቴ ገሺ አውደ ርዕዩ በክልሉ ተኪ ምርቶች ላይ የተሰማሩ ኢንዱስትሪዎችን ያነቃቃል። አውደ ርዕዩ በተጨማሪም በክልሉ ያሉትን ዘርፈ ብዙ የኢኮኖሚ አቅሞች በማስተዋወቅ ወደ ልማት እንዲገቡ መልካም አጋጣሚን እንደሚፈጥር ገልጸዋል። በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች ‎በአውደ ርዕዩ ላይ እንደሚሳተፉ ገልፀው፤ ኢንዱስትሪዎቹ የእርስ በርስ የተሞክሮ ልውውጥ የሚያደርጉበት እና ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት የሚገመገምበት መሆኑን ተናግረዋል። ከ2014 ዓ.ም ጀምሮ እየተካሄደ የሚገኘው የኢትዮጵያ ታምርት አውደ ርዕይ የሀገር ውስጥ ተኪ ምርቶችን በማበረታታት የወጪ ፍላጎትን በራስ ምርት ለመሸፈን የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት ጉልህ ሚና እየተጫወተ ነው ብለዋል። ‎በክልሉ የማዕድን፣ የግብርና፣ የተፈጥሮ ሀብት እና የአገልግሎት ዘርፎችን በቅንጅት በመምራት ለኢንዱስትሪው ምቹ የማድረግ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አስረድተዋል።      
የአርብቶ አደሩን ማሕበረሰብ ህይወት በዘላቂነት ለመለወጥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ስኬታማ ናቸው
Aug 18, 2026 121
ጂንካ፤ ነሐሴ 12/2018(ኢዜአ) ፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኙ አርብቶ አደሮችን ህይወት በዘላቂነት ለመለወጥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የዲላ ክላስተር አስተባባሪና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር)፤ በደቡብ ኦሞ ዞን በና-ፀማይ ወረዳ ወይጦ ክላስተር በአርብቶ አደሮች በኩታ ገጠም የለማውን የሽንኩርት ማሳ ጎብኝተዋል።   ዶክተር መሪሁን በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ አርብቶ አደሩን ማህበረሰብ ከእንስሳት እርባታው በተጨማሪ በእርሻ ስራ በማሰማራት የገቢ ምንጫቸውን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው። የክልሉ መንግስት የአርብቶ አደሮችን ህይወት በዘላቂነት ለመለወጥ የሚያስችሉ ተግባራት በማከናወን ስኬታማ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ነው የጠቆሙት። ማሕበረሰቡን ከከብት እርባታው በተጨማሪ በእርሻ ስራ በማሰማራት ወደ ብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፍ የማሸጋገር ስራ በትኩረት በመሰራቱ ውጤቱ መመዝገቡን ነው የተናገሩት። ለዚህም በኩታ ገጠም እርሻ የተሰማሩ አርብቶ አደሮች ማሳያ ናቸው ያሉት ዶክተር መሪሁን፥ የማህበረሰቡን ኑሮ ለማሻሻል የሚደረጉ ድጋፎች ቀጣይነት እንደሚኖራቸው ነው ያረጋገጡት። በአርብቶ አደሩ አካባቢ እምቅ የግብርና አቅም ያለ በመሆኑም ከማህበረሰቡ አልፎ ለሀገር ኢኮኖሚ እድገት ማዋል እንደሚቻል የገለጹት ደግሞ የደቡብ ኦሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማዕከል ማሊኮ ናቸው።   ይህን ሀብት በማልማት አርብቶ አደሩን ከተረጅነት ለማውጣት ሰፋፊ የግብርና ልማት ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙም ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅትም አርብቶ አደሩ ማህበረሰብ ከጠባቂነት ወደ አምራችነት በመሸጋገር ሀብት በማፍራት ላይ መሆኑን ጠቁመው ፥ የሚደረገው ድጋፍም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የደቡብ ኦሞ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ በበኩላቸው፤ በዞኑ ያሉ ሀብቶችን በማቀናጀት ለማልማት በተደረገው ጥረት ለውጥ መጥቷል።   በአካባቢው የሚገኘውን የወይጦን ወንዝ በመጥለፍ እንዲሁም የከርሰ ምድር ውሃን በማውጣት ከ 2 ሺህ 400 ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ ሽንኩርት በመስኖ እየለማ እንደሚገኝም ነው የተናገሩት። በዚህም ከ2 ሺህ 700 በላይ አርብቶ አደሮች እየተሳተፉ ሲሆን ማህበረሰቡን ከተረጅነት በማላቀቅ ሀብት እንዲያፈራ ማድረግ እንደተቻለም ገልጸዋል። ከዚህ ቀደም በአካባቢው ግብርና ስራ እምብዛም እንደማይታወቅ ጠቁመው የአካባቢው ማህበረሰብ በተደጋጋሚ ለድርቅና ተያያዥ ችግሮች ተጋላጭ ይሆን እንደነበር አስታውሰዋል።   በበና-ፀማይ ወረዳ ወይጦ ክላስተር የእንጨቴ ቀበሌ አርብቶ አደር የሆኑት ተክሉ ዘውዴ እና መንግስቱ ቦንዳ ፤በኩታ ገጠም ሽንኩርትን ጨምሮ ሌሎች አትክልቶችን በማልማት ከእጅ ወደ አፍ የነበረው ኑሯቸው በእጅጉ እየተሻሻለ መምጣቱን ጠቁመዋል።   በሄክታር ከ250 እስከ 300 ኩንታል ምርት እያገኙ እንዳሉ ጠቁመው፥ የገበያ ትስስር በመፍጠር ረገድም ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑንም ተናግረዋል።  
የኮሪደር እና የወንዝ ዳር ልማቶች  በአእምሮ እና በአካል የበለጸገ ትውልድን ለመገንባት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው
Aug 18, 2026 118
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የተገነቡ የኮሪደር እና የወንዝ ዳርቻ ልማቶች ገጽታን ከመቀየር ባለፈ በአእምሮ እና በአካል የበለጸገ ትውልድን ለመገንባት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ነዋሪዎች ገለጹ። በአዲስ አበባ ከተማ የተከናወኑ የኮሪደር እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራዎች የከተማዋን መሠረተ ልማት ከዘመኑ ጋር በማስተሳሰር፣ የነዋሪዎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ደህንነት ማሻሻልና አረንጓዴ ቦታዎችን በማስፋፋት ትርጉም ያለው ለውጥ ማምጣት ችለዋል።   ከተማዋን ለቱሪስቶች ማራኪ ከማድረጉም በላይ በወንዞች ዳርቻዎች ላይ የነበሩ የጎርፍ አደጋ ስጋቶችን በመቀነስ ህብረተሰቡ ንጽህናው የተጠበቀ የመኖሪያ እና መዝናኛ ስፍራዎችን እንዲያገኝ አድርጓል። በዚህም ዘላቂ የከተማ ልማት እውን እንዲሆን በማስቻል የዜጎችን የኑሮ ጥራት ከፍ አድርጓል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት የመዲናዋ ነዋሪዎች፣ የኮሪደር እና የወንዝ ዳርቻዎች ልማት ሥራ ከፍተኛ የገጽታ ግንባታ ከመፍጠሩም በላይ ሁሉንም ተጠቃሚ ማድረግ የቻለ አካታች ልማት መሆኑን ተናግረዋል።   የአዲስ አበባ ነዋሪ ሲሳይ ተስፋዬ እንደገለጹት፤ የተከናወኑት ግዙፍ የልማት ሥራዎች ለንባብ፣ ለምርምር እና ለህፃናትና ወጣቶች መዝናኛ ያላቸው ፋይዳ ከፍተኛ ነው። በተለይም የቱሪዝም ፍሰትን በማሳደግና የውጭ ምንዛሬ ገቢን በመጨመር ረገድ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት እምነታቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም ህብረተሰቡ የተገነቡት መሠረተ ልማቶች ያላቸውን ዘርፈ ብዙ ፋይዳ በመገንዘብ በባለቤትነት ስሜት ሊንከባከባቸውና ሊጠብቃቸው እንደሚገባ አንስተዋል።   አልማዝ ባሻ በበኩላቸው፣ መንግሥት በከተማዋ ያከናወናቸው የልማት ሥራዎች አዲስ አበባን ዘመናዊ፣ ጽዱ እና ለኑሮ ተስማሚ እንዳደረጓት ገልጸዋል። ሀገር ተረካቢው ትውልድም የእረፍት ጊዜውን በመናፈሻዎችና በስፖርት ማዘውተሪያዎች የሚያሳልፍበት ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም ጠቁመዋል። ይህም መንግስት ለአሁን እና ለቀጣዩ ትውልድ የምትሆን ሀገር እየገነባ መሆኑን ያሳያል ብለዋል። ደስታ መአረንዳ እና አዱኛ ጌትነት እንዳሉት በአዲስ አበባ አሁን ላይ የሚገባትን ውበት እና ክብር መጎናጸፍ ችላለች።   ይህ ሊሆን የቻለው በአእምሮ እና በአካል የበለጸገ ትውልድን ለመፍጠር ታሳቢ ያደረጉ ሁለንተናዊ የከተማ ልማት ሥራዎች በስፋት በመሰራታቸው መሆኑን አንስተዋል።   የወንዝ ዳርቻ፣ መጽዳት ቤቶችና ቆሻሻ አወጋገድ በመስተካከሉ መጥፎ ሽታዎችን በማስቀረት ለነዋሪዎች፣ ለህፃናት፣ ለሁሉም ህብረተሰብ ክፍሎች እንዲሁም ለቱሪስቶችም ጭምር ዘመኑን የሚመጥን ከተማ ተፈጥሯል ያሉት ደግሞ ክብሩ ወልደሰንበት እና ወልዱ ግርማ ናቸው።   መንግስት ቀደም ሲል የተዘነጉ ጉዳዮች ላይ ከፍተኛ በጀት በመመደብ ለዜጎች የኑሮ ዘይቤ መሻሻል የሚያደርገው ቁርጠኛ አካሄድ የሚደነቅ መሆኑንም ተናግረዋል።  
በዞኑ የተገነቡ የመንገድ መሰረተ ልማቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያሳደጉ ይገኛሉ
Aug 18, 2026 112
ገንዳ ውኃ፣ ነሐሴ 12/2018 (ኢዜአ):- በምዕራብ ጎንደር ዞን የተገነቡ የድልድይ መሰረተ ልማቶች፣ የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግ እንዳስቻሉ ነዋሪዎች ገለጹ። በምዕራብ ጎንደር ዞን በቋራ እና መተማ ወረዳዎች ህብረተሰቡን በማሳተፍ ከሁለት መቶ አርባ ኪሎ ሜትር በላይ መንገድ እና አምስት የኮንክሪትና ተንጠልጣይ ድልድዮችን በመገንባት ለአገልግሎት ማብቃት መቻሉም ተገልጿል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት የቋራ ወረዳ ነዋሪ አቶ አያሌው መኮንን እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል በክረምት ወቅት ከመተማ ወረዳ ጋር ለመገናኘት አስቸጋሪ እንደነበር ይገልፃሉ። በአሁን ወቅት ግን በሽንፋ ወንዝ ላይ የተገነባው ተንጠልጣይ ድልድይ፣ የግብርና ምርቶችን ወደ ማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ ያጋጥማቸው የነበረውን የትራንስፖርት ችግር እንደቀረፈላቸው ነው የሚናገሩት። የመንገድ መሠረተ ልማቱ መገንባት ነዋሪዎቹ በኢኮኖሚያዊና በማህበራዊ ጉዳዮች ያላቸውን ግንኙት ይበልጥ ለማጠናከር ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም አክለዋል። ሌላው አስተያየት ሰጪ የመተማ ወረዳ የመሸሃ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ደስታው ዳኘው በበኩላቸው፣የተገነባው የጠጠር መንገድ ከዚህ ቀደም በክረምትና በበጋ ለመንቀሳቀስ ይደርስብን የነበረውን ችግር የፈታ ነው። በተለይ በክረምት ወቅት እናቶችና ህጻናት ወደ ጤና ተቋማት ለመሄድ ያጋጥማቸው የነበረውን ከፍተኛ እንግልት እንዳስቀረም ነው ያስረዱት ። የመንገዱ መገንባት በአካባቢው የንግድ እንቅስቃሴ እንዲቀላጠፍና የሸቀጦች አቅርቦት እንዲሻሻል ማድረጉን የገለፁት ደግሞ በቋራ ወረዳ ሽመለጋራ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ እመቤት ደስታው ናቸው። ቀደም ሲል እናቶች ለወሊድና ለህክምና ወደ ጤና ተቋማት በሰው ሸክም ይወሰዱ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ግን ተሽከርካሪዎች እስከ መንደራቸው ድረስ ለመግባት በመቻላቸው ችግሩ መቃለሉን ነው የገለጹት። የምዕራብ ጎንደር ዞን መንገድና ትራንስፖርት መምሪያ የዲዛይንና ኮንስትራክሽን አስተዳደር ቡድን መሪ አቶ ጥላሁን አበበ፣ የመንግሥት ትኩረት የህብረተሰቡን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ምላሽ መስጠት መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ህብረተሰቡን በማሳተፍ ከሁለት መቶ አርባ ኪሎ ሜትር በላይ መንገድን ጨምሮ አምስት የኮንክሪትና ተንጠልጣይ ድልድዮችን በመገንባት ለአገልግሎት ማብቃት መቻሉን አስረድተዋል። የተገነቡት መንገዶች ወረዳዎችንና የገጠር ቀበሌዎችን እርስ በእርስ የሚያገናኙ በመሆናቸው የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉንም አቶ ጥላሁን አረጋግጠዋል።
የስራ አጥነትን በስራ ፈጠራ ያሸነፉ ወጣቶች
Aug 18, 2026 139
በጅማ ከተማ አስተዳደር ያለውን የስራ አጥነት ቁጥር ለመቀነስ ወጣቶችን በተለያዩ የስራ ፈጠራ ጥቃቅንና አነስተኛ ዘርፎች በማደራጀት አበረታች እና ተጨባጭ ለውጥ በማስመዝገብ ላይ ይገኛል። ግብርና እና የግብርና ውጤቶች ማቀነባበር፣ የእንጨት እና ብረታብረት ስራዎች፣ የጎጆ ኢንዱስትሪ፣ አገልግሎት እና ንግድ እንዲሁም የአካባቢ ጥበቃ እና መልሶ ጥቅም ላይ ማዋል የመሳሰሉት ደግሞ ወጣቶቹ ከተደራጁባቸው መስኮች ዋነኞቹ ናቸው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ወጣቶች እንዳሉት፤ ስራ ማጣት የሚያስከትለውን ተስፋ መቁረጥ በፈጠራ ስራ በመተካት በራሳቸው ስራ ተሰማርተዋል። በዚህም የራሳቸውንና የቤተሰቦቻቸውን ህይወት ከመቀየር ባለፈ፣ በከተማዋ ለሚገኙ ሌሎች ወጣቶችም የከተማዋን ኢኮኖሚ የሚያንቀሳቅስ ተስፋ ሰጪ ሞዴል መሆን ችሏል። የከተማዋ ነዋሪ ፎዚያ ከድር ከዓመት በፊት በሥራ ፍለጋ ተስፋ ቆርጣ እንደነበር ትናገራለች። ዛሬ ግን በከተማዋ በተመቻቸላት የጎጆ ኢንዱስትሪ ዕድል የእንጨት ቅርጻ ቅርጽ ሥራን በመስራት ራሷን ከመቻል አልፋ ለሌሎችም የሥራ ዕድል መፍጠር ችላለች።   ሌላኛው ወጣት አብዱረዛቅ ሸውሞሎ አስተዳደሩ ባመቻቸው የጎጆ ኢንዱስትሪ ስራ ውስጥ ከሶስት ጓደኞቹ ጋር በመደራጀት የለውዝ ቅቤ ማምረት ስራ ላይ ተሰማርቷል። የመስሪያ ቦታን ጨምሮ አስፈላጊው ድጋፍ የተደረገላቸው መሆኑን ገልጾ፤ የሚያዘጋጁት የምግብ ግብዓት ተፈትሾ ጥራቱ የተረጋገጠ በመሆኑ፣ ምርታቸውን በሙሉ እምነት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆን እንደቻሉ ተናግረዋል።   ይህ ዓይነቱ የጥራትና የድጋፍ ትስስር የስራ ፈጠራ እንቅስቃሴያቸው ዘላቂ እንዲሆን ማስቻሉን ገልጾ፤ በዚህም ከራስ አልፎ ለሌሎች የስራ ዕድል ፈጥረዋል።   ጂቱ አብዶ እና ሂክማ መሀመድናስርም የዚሁ ዕድል ተጠቃሚ ናቸው።   ከጓደኞቻቸው ጋር በመደራጀት ሰርተው መለወጣቸውን ገልጸው፤ በዚህም ከራስ አልፈው ቤተሰቦቻቸውን በመርዳት ላይ ይገኛሉ።   መንግስት ወጣቶች ላይ ትኩረት አድርጎ መስራቱ የሚያስደስት በመሆኑ በቀጣይም የበለጠ ሰርተን ለሌሎች ለመትረፍ እንተጋለን ብለዋል ወጣቶቹ።   በጅማ ከተማ የስራ ዕድል ፈጠራ እና ክህሎት ጽህፈት ቤት የስራ ዕድል ፈጠራ ቡድን መሪ አቶ አሸናፊ ግርማ በበኩላቸው በከተማዋ ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ በርካታ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል።   በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የጎጆ ኢንዱስትሪን ጨምሮ በ3ሺህ 279 ማህበራት ለ31 ሺህ 659 ዜጎች የስራ ዕድል ተፈጥሯል። ለማህበራቱ ውጤታማነትም የብድር እና የመስሪያ ቦታን ጨምሮ አስፈላጊ ነገሮች መመቻቸታቸውንም አብራርተዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም 4 ሺህ 100 ማህበራትን በማደራጀት ለበርካቶች የስራ ዕድል ለመፍጠር መታቀዱን ጠቅሰው፤ ወጣቶች የሚያነሱትን የገበያ ትስስር ጥያቄ ምላሽ ለመስጠትም ከባለድርሻ አካላት ጋር በስፋት እየተሰራ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም