ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ለህብረተሰቡ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚያችሉትን ተግባራት እያከናወነ ነው
Aug 1, 2026 132
ሀረር፤ ሐምሌ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ለህብረተሰቡ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችሉትን ተግባራት እያከናወነ መሆኑን አስታወቀ። በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሐረሪ ሪጅን ጽህፈት ቤት ዘመናዊ ህንጻ ግንባታ ማስጀመርያ ስነ ስርዓት አካሂዷል። በግንባታ ማስጀመሪያው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ተወካይ ለምለም ምስጋናው፣ የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈጻሚ ብርጋድየር ጀነራል ኢንጂነር ሰጠኝ ሊኪሳ እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል። ለምለም ምስጋናው በወቅቱ እንደገለጹት ተቋሙ ለህብረተሰቡ ቀልጣፋና አስተማማኝ አገልግሎት ለመስጠት እየተጋ ነው ። ለዚህም የተለያዩ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ጠቁመው በሐረሪ ክልል የሚገነባው ህንጻም የአገልግሎት አሰጣጡን ይበልጥ የሚያጎለብት መሆኑን አመላክተዋል። አዲስ የሚገነባው የሐረሪ ሪጅን ጽህፈት ቤትም 10 ወለሎች ያሉትና 2 ቢሊየን በሚጠጋ ብር የሚገነባ መሆኑን ተናግረዋል ። የግንባታ ስራው በ900 ቀናት እንደሚጠናቀቅ ጠቁመው፤ የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ግንባታውን እንደሚያከናውንም አስታውቀዋል። የህንጻው መገንባት በሪጅኑ የሚሰጠውን አገልግሎት ወደተሻለ ደረጃ ከፍ እንዲል ያስችለዋል ያሉት ደግሞ የአገልግሎትቱ የሐረሪ ሪጅን ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዳይሪክተር አቶ ካሊድ ጠሃ ናቸው። የመከላከያ ኮንስትራክሽን ኢንተርፕራይዝ ዋና ስራ አስፈጻሚ ብርጋድየር ጀነራል ኢንጂነር ሰጠኝ ሊኪሳ በበኩላቸው ኢንተርፕራይዙ በሀገሪቱ በርካታ የህንጻ፣ የመንገድና ሌሎች ግንባታዎችን እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል ። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የሐረሪ ሪጅን ጽህፈት ቤት ዘመናዊ ህንጻ ግንባታንም በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ በፍጥነትና በጥራት እንደሚያከናውን አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም እና የመሠረተ-ልማት ግንባታዎች ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ማዕከል አድርገዋታል
Aug 1, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም እና የመሠረተ-ልማት ግንባታዎች ሀገሪቷን ተመራጭ ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ማዕከል እንዳደረጓት የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁ የህንድና የፊንላንድ አምባሳደሮች ገለጹ። አምባሳደሮቹ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤን ጨምሮ በዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ላይ እያከናወነቻቸው ያሉትን እርምጃዎች አድንቀዋል። የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁት በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የኢትዮጵያ ቀጣይነት ያላቸው ሪፎርሞች እና ትላልቅ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች ሀገሪቱን ለዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንት ተመራጭ መዳረሻ እያደረጓት መሆኑን ገልጸዋል። በቢሾፍቱ እየተገነባ ያለው አዲሱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያን ጨምሮ የኢትዮጵያ ፈጣን የከተሞች ለውጥ እና ትላልቅ የመሠረተ ልማት ዝርጋታዎች የውጭ ኢንቨስትመንት የመሳብ አቅሟን የሚያሳድጉ መሆኑንም አንስተዋል። ኢትዮጵያ የዲጂታል ዘርፉን ጨምሮ የኢንቨስትመንት ምህዳሩን ለማስፋት ያከናወነቻቸው ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን ነው አምባሳደሩ የጠቀሱት። ለአብነትም በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ ሰው ሰራሽ አስተውሎት እና በፋይናንስ ቴክኖሎጂ ዘርፎች በኢትዮጵያ ትልቅ አቅም መፈጠሩንም አመልክተው፤ ሪፎርሙን ጨምሮ በኢትዮጵያ የተፈጠረው ምቹ የኢንቨስትመንት ምህዳር የህንድ ኩባንያዎችን እየሳበ መሆኑንም አስረድተዋል። አዳዲስ የህንድ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ በሂደት ላይ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ከራሷ አልፎ ለቀጣናው ሰላምና መረጋጋት እየተጫወተች ያለችውን ሚናም አድንቀዋል። በኢትዮጵያ የተካሄደው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ እና የሕዝቡ ተሳትፎ የኢትዮጵያን የዴሞክራሲ ስኬታማ ጉዞ ያንጸባረቀ መሆኑን አመልክተው፤ ችግሮችን በውይይት ለመፍታት ተግባራዊ መደረግ የተጀመረው ሀገራዊ ምክክርም ትልቅ እርምጃ መሆኑን ተናግረዋል። ሂደቱ ኢትዮጵያ ልዩነቶችን እየፈታች ብሔራዊ አንድነቷን ለማስጠበቅ እና የልማት ጎዳናዋን ለማስቀጠል ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁት የፊንላንድ አምባሳደር ሲኒካ አንቲላ በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ በየዘርፉ እየታየ ያለው ለውጥ አስደማሚ መሆኑን ገልጸዋል። ፊንላንድና ኢትዮጵያ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በፈጠራ ሥራዎች እና በቴክኖሎጂ ትብብራቸውን ለማጠናከር ሰፋፊ ዕድሎች እንዳሏቸው አብራርተው፤ በልማት ትብብር በጋራ መሥራታቸውንም ይቀጥላሉ ብለዋል። ፊንላንድ ከኢትዮጵያ ጋር በንግድ እና በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረቱ ኢንቨስትመንቶች ላይ ያላትን አጋርነት እንደምታጠናክርም አረጋግጠዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኢትዮጵያ የቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪውን በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል
Aug 1, 2026 127
ሆሳዕና፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲቲዩት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪውን በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን ገለፀ። የቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ኢንስቲትዩት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገቡ ተስፋ ሰጪ ውጤቶችንና የወደፊት እቅዶችን በሆሳዕና ከተማ እያገመገመ ነው። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ነጋሽ እንደተናገሩት፤ መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉ የሰጠው ትኩረት ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ለማድረግ አስተዋፅዖ እያበረከተ ይገኛል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኢትዮጵያን የቱሪዝም ሆስፒታሊቲ ኢንዱስትሪ በመደገፍ በኩል ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን አስተማማኝና ዘላቂ የኢኮኖሚ መሰረት ከማድረግ ባለፈ ለስራ ፈጠራ እንዲውል እየተሰራ መሆኑን ነው ያብራሩት። በአሁኑ ወቅትም የቱሪስት መስሕቦችን የማደስ፣ አዳዲስ የቱሪዝም መሰረተ ልማቶችን የማስፋፋት ስራ መከናወኑ የኢትዮጵያን የኮንፍረንስ ቱሪዝም ተመራጭነት እያሳደገ ነው ይህም የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች ቁጥር እንዲጨምር አድርጓል ነው ያሉት። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ1 ነጥብ 4 ሚሊየን በላይ የውጭ ጎብኚዎች እንዲሁም ከ 50 ሚሊየን በላይ የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች የተለያዩ መስሕቦችን መጎብኘታቸውን አስታውቀዋል። ኢንስቲትዩቱ በሀገሪቱ በቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ሙያዎች ዜጎችን ዓለም አቀፍ ደረጃን በጠበቀ መልኩ በማሰልጠንና ችግር ፈቺ የጥናትና ምርምር ስራዎችን በማከናወን የበኩሉን እየተወጣ ነው ብለዋል። በሆሳዕና ከተማ ለሁለት ቀናት እየተካሔደ ባለው የምክክር መድረክ የ2019 በጀት ዓመት እቅድ ላይ ውይይት እንደሚደረግ ተገልጿል።
የአማራ ክልል ምክር ቤት ለአዲሱ በጀት ዓመት ከ402 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ በጀት መርምሮ አጸደቀ
Aug 1, 2026 124
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ የአማራ ክልል ምክር ቤት በ2019 በጀት ዓመት ለሚካሔዱ የልማት ዕቅዶች ማስፈጸሚያ የሚውል ከ402 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ በጀት መርምሮ አጽድቋል። የክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 12ኛ መደበኛ ጉባኤ በሦስተኛ ቀን ውሎው በተለያዩ አጀንዳዎች ዙሪያ በመምከር እና የአዲሱነ በጀት ዓመት የዕቅድ ማስፈጸሚያ በጀት በማጽደቅ ተጠናቋል። የክልሉ ገንዘብ ቢሮ ኃላፊ አታላይ ጥላሁን የበጀት ረቂቁን ባቀረቡበት ወቅት እንዳሉት፤ በጀቱ የክልሉን ህዝብ የመልማት ፍላጎት መሰረት ያደረገ ነው። ከበጀቱ ውስጥ ከ286 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ የሚሆነው በክልሉ ከሚሰበሰብ ገቢ የሚሸፈን ሲሆን 111 ቢሊየን የሚጠጋው ደግሞ ከፌደራል መንግስት ጥቅል የቀመር መደበኛ ድጋፍ የሚገኝ ነው ብለዋል። ቀሪው ከዘላቂ ልማት ግቦችና መሰል የፋይናንስ ምንጮች በሚገኝ ሀብት የሚሸፈን እንደሆነም ተናግረዋል። የበጀት ድልድሉ ሊኖሩ የሚችሉ ለውጦችን፣ የመዋቅር ማሻሻያዎችን፣ ብሎም ወረዳዎችና ከተሞች የድህነት ተኮር ዘርፍ ያለባቸውን የካፒታል በጀት ውስንነት መሰረት የተደረገ ነው ብለዋል። የተመደበው በጀት ካለፈው በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀር በ176 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር በላይ ወይም 78 ነጥብ 8 በመቶ ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል። በጀቱ የክልሉን ህዝብ የላቀ የልማት ጥያቄ ፍላጎት መሰረት በማድረግ የቀረበ እንደሆነም አብራርተዋል። የቀረበውን በጀት የህዝብን የልማት ጥያቄ በአግባቡ ሊመልስ በሚችል አግባብ ለታለመለት ዓላማ በቁጠባ ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ለስኬታማነቱም በየደረጃው ያለው ባለድርሻ አካል የድርሻውን መወጣት እንዳለበት አሳስበዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም የአምራች ኢንዱስትሪ ተወዳዳሪነትና የቡና ወጪ ንግድን አሳድጓል
Aug 1, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም የአምራች ኢንዱስትሪውን ተወዳዳሪነትና የቡና ምርታማነትና ወጪ ንግድን በከፍተኛ በሁኔታ ማሳደጉን አምራቾችና ላኪዎች ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ በሰጡት ማብራሪያ ሀገራዊ የሪፎርም ስራ ለውጭ ምንዛሬ ግኝት ስኬቶች ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን መግለፃቸው ይታወሳል። ይህም በዘንድሮው ዓመት ከቡና ኤክስፖርት ብቻ 3 ነጥብ 1 ቢሊየን ዶላር ማስገኘት መቻሉን መግለፃቸውም እንዲሁ። የኦሮሚያ የቡና አቅራቢዎች ማህበር ምክትል ፕሬዝዳንት እና የከብሬ ለኬ ቡና ላኪ ድርጅት ባለቤት ፈጠነ የኋላእሸት ለኢዜአ እንደገለጹት ከዚህ ቀደም በዘርፉ የነበሩ የፖሊሲ ክፍተቶች በቡና ምርትና ምርታማነት ላይ ተጽዕኖ ፈጥረው ቆይተዋል። ተግባራዊ የተደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ለዘርፉ ተዋናዮች መልካም እድል መፍጠሩን ጠቁመው ይህን ተከትሎም የቡና ኤክስፖርት በመጠንም ሆነ በገቢ ከፍ እያለ መምጣቱን ገልጸዋል። የተደረገው ማሻሻያ በእሴት ሰንሰለቱ ላይ ያሉ ችግሮችን መለየት ማስቻሉን ይህም ቡና በቀላሉ ወደ ውጭ እንዲላክ ማድረጉን አስታውቀዋል። በተጨማሪም አሰራሮች ዲጂታላይዝ መደረጋቸው ዘርፉን ዘመናዊ እንዳደረገውና ለቡና ወጪ ንግድ እድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማበርከቱን ተናግረዋል። ሪፎርሙን ተከትሎ በተሰሩ ስራዎች የቡና ምርታማነትና ጥራት በመጨመሩ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪነትን ማሳደግ መቻሉንም ገልጸዋል፡፡ በተለይም ባለፉት ሶስት ዓመታት የቡና ወጪ ንግድ በየዓመቱ በመጠንም ሆነ በገቢ ከፍተኛ እድገት ማሳየቱን አብራርተዋል። በቀጣይም መንግስትና የዘርፉ ተዋናዮች ትብብራቸውን አጠናክረው ከቀጠሉ የወጪ ንግድ አፈፃፀምንና የዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነትን በዘላቂነት ማረጋገጥ እንደሚቻል አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ማሽነሪና መለዋወጫ አምራቾች ማህበር ፀሀፊ እና የፅዮን ኢንደስትሪያል ኢንጂነሪንግና ብረታ ብረት ኢንተርፕራይዝ ባለቤት ዮሃንስ ግርማ በበኩላቸው መንግስት በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለአምራች ዘርፉ ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱን ገልጸዋል። በተለይም ተኪ ምርቶችን ለሚያመርቱና የወጪ ንግድ ኤክስፖርት ምርትን ለማሳደግ ለሚሰሩ አምራቾች ውጤታማ የሚያደርጉ የተለያዩ ድጋፎች እየተደረጉ መሆኑን አስታውቀዋል። ለአምራች ዘርፉ በተሰጠው ትኩረትና እየተደረገ ባለው አጠቃላይ ድጋፍ የምርት ጥራትና ምርታማነትን በማሳደግ የዘርፉን ተወዳዳሪነት ማጎልበት መቻሉንም ጨምረው አስታውቀዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል እንደገለጹት፤ የኢንዱስትሪዎችን ችግር ከመለየት ጀምሮ በዘላቂነት ተወዳዳሪ ሊሆኑ የሚችሉበት አሰራር ተዘርግቷል። የአምራች ኢንዱስትሪ ችግሮችን ለመፍታት የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በዘርፉ ከፍተኛ ውጤቶች መመዝገባቸውንም አመላክተዋል። ይህም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን የፋይናንስ ማነቆ በመፍታት ቀደም ሲል 40 ቢሊየን ብር የነበረውን የብድር መጠን ወደ 115 ቢሊየን ብር ከፍ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። በዚህም የኢንዱስትሪዎቻችን ተወዳዳሪነት፣ ምርታማነት፣ ትርፋማነትና የመስፋፋት ዕድል ከፍ እያለ መምጣቱን ገልጸዋል።
በባሌ ዞን ከበልግ እርሻ እስካሁን 6 ነጥብ 9 ሚሊየን ኩንታል ምርት ተሰብስቧል
Aug 1, 2026 230
ሮቤ፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን በበልግ ወቅት ከለማወ መሬት ከ6 ነጥብ 9 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በዞኑ በሜካናይዜሽን የታገዘው የሰብል ስብሰባ ሒደት በድህረ ምርት ወቅት ሊያጋጥም የሚችለውን የምርት ብክነት ለመቀነስ ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለውም ተገልጿል። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አልይ መሐመድ እንዳሉት፤ በዞኑ በበልግ ወቅት ከለማው 277 ሺህ 182 ሄክታር መሬት ውሰጥ እስካሁን በተደረገ ጥረት ስድስት ነጥብ ዘጠኝ ሚሊየን ኩንታል ምርት ተሰብስቧል። ይህም በሰብል ከተሸፈነው አጠቃላይ መሬት 90 በመቶውን እንደሚሸፍን ተናግረዋል። የምርት አሰባሰብ ሂደቱ ተጠናክሮ መቀጠሉንና በአጠቃላይ በምርት ዘመኑ ከለማው መሬት ስምንት ነጥብ ሦስት ሚሊየን ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። በበልግ ወቅት ከለማው መሬት 107 ሺህ ሄክታሩ በስንዴ ሰብል መልማቱን ጠቁመው እስከ አሁን ከተሰበሰበው 82 ሺህ ሄክታር መሬት 3 ነጥብ 2 ሚሊየን ኩንታል የስንዴ ምርት መሰብሰቡን አስታውቀዋል። የደረሱ ሰብሎችን ወቅቱን ካልጠበቀ ዝናብ ለመታደግ በኮምባይነር እየተደረገ ካለው የመሰብሰብ ስራ በተጓዳኝ በጥቃቅን ማሽነሪዎችና በሰው ጉልበትም እየተሰበሰበ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም በመካናይዜሽን ሰብልን ለመሰብሰብ የሚደረገው ጥረት ሊደርስ የሚችለውን የምርት ብክነት ከማስቀረቱም በላይ ጥራቱን የጠበቀ ምርት ለገበያ ለማቅረብ የጎላ አስተዋፅኦ እንዳለውም አክለዋል። በዞኑ በበልጉ ወቀት በተለያዩ የሰብል አይነቶች ከተከሸፈነው ማሳ 73 በመቶ የሚሆነው የተሻሻሉ የግብርና አሰራሮችና ሙሉ ፓኬጆችን በመጠቀም በኩታ ገጠም የለማ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አብዱልሀኪም አልይ ናቸው። በዞኑ በመኸር፣ በበልግና በመስኖ አማራጮች ከ900 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት እንደሚለማና፣ ከ20 ሚሊየን ኩንታል በላይ ዓመታዊ ምርት እንደሚጠበቅ አመልክተዋል። ከሲናና ወረዳ አርሶ አደሮች መካከል ሐጅ ሳፊ አህመድ በሰጡት አስተያየት፤ ሰብልን በኮምባይነር በመሰብሰብ ይደርስ የነበረውን ብክነት ማስቀረት መቻላቸውን ተናግረዋል። ከአካባቢያቸው አርሶ አደሮች ጋር በመቀናጀትም በኩታገጠም አሰራር በመታገዝ መሬታቸውን ማልማታቸው ምርታማነታቸውን እንዳሳደገላቸው አመልክተዋል። በኦሮሚያ ክልል በዝናብ ውኃ አማራጭ በመኽርና በልግ አዝመራ በዓመት ሁለቴ ከሚመረትባቸው አካባቢዎች አንዱ ባሌ ዞን ነው። በዞኑ ከሚያዝያ ወር መጨረሻ እስከ ነሐሴ መገባደጃ ያለው ጊዜ የበልግ የምርት ወቅት መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።
ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ንግድ ትስስርና ዕድገት ቁልፍ ሀገር ነች
Aug 1, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በቀጣናዊ እና አህጉራዊ የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲሁም በንግድ እንቅስቃሴ ውስጥ ወሳኝ ሚና እየተጫወተች የምትገኝ ቁልፍ ሀገር መሆኗን በአፍሪካ የንግድና የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት አድርጎ የሚሠራው 'ትሬድ ካታሊስት አፍሪካ' ገለጸ። ኢትዮጵያ ያሏት የታሪክ፣ የስነ-ህዝብ፣ የመሰረተ ልማት እና የጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ ፀጋዎች በቀጣናው ኢኮኖሚያዊ ትስስርን ለማፋጠን ወሳኝ ድርሻ እንድትጫወት አስችለዋታል፡፡ እንዲሁም የሃይል እና ትራንስፖርት መረቦችን ለመዘርጋትና በአህጉር ደረጃ የፖሊሲ እና የዲፕሎማሲ አቅጣጫዎችን ለመቀየስ የሚያስችላትን የጎላ ድርሻ ይሰጣታል። የ'ትሬድ ካታሊስት አፍሪካ' ዋና ሥራ አስፈጻሚ አደሬ አዳንኮ ኒያንጎ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ ሰፊ የሕዝብ ቁጥር፣ ትልቅ ኢኮኖሚና በርካታ አምራች ወጣቶች ያላት ሀገር መሆኗን ገልጸዋል። ይህ መልካም አጋጣሚ ሀገሪቱ ለአፍሪካ የኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንድታበረክትና ተጽዕኖዋን እንድታሰፋ የሚያስችላት መሆኑንም አስታውቀዋል። በሀገሪቱ ውስጥ በርካታ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ዘርፎች ለልማትና ለስኬት ሰፊ እድል ይዘው እንደሚገኙ ጠቅሰው፤ በተለይም በግብርና እና በግብርና ማቀነባበር መስኮች ላይ ያሉ ሰፊ ዕድሎችን አንስተዋል፡፡ እንዲሁም እንደ ጤና፣ ትምህርት እና የፋይናንስ አገልግሎቶች ባሉ ቁልፍ ዘርፎችም ትልቅ የእድገት አቅም መኖሩን ጨምረው አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ትኩረት እየተሰጣቸው ያሉት ወሳኝ ማዕድናት የኢትዮጵያን ሀገራዊ ብልጽግና በጽኑ መሰረት ላይ ለማቆም እንደሚያስችሉ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በቀጣናዊ እና አህጉራዊ የኢኮኖሚ እድገት እንዲሁም በንግድ እንቅስቃሴ ውስጥ ወሳኝ ሚና እየተጫወተች የምትገኝ ቁልፍ ሀገር ናት ብለዋል። በዩናይትድ ኪንግደም በሚገኘው ዓለም አቀፍ ገለልተኛ የፖሊሲ እና ጥናት ተቋም (ODI) ዋና ተመራማሪ ማክሲምን ዲባራ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ አህጉር በፍጥነት እያደጉ ካሉ የኢኮኖሚ ማዕከላት አንዷ መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ የኢኮኖሚ እድገት እያሰመዘገበች እንደምትገኝ አንስተው፤ በተለይም በግብርና እና በአምራች ዘርፎች የሚታየው የእድገት እንቅስቃሴ ከፍተኛ መሆኑን አስታውቀዋል ይህ እድገት ኢትዮጵያ የባህረ ሰላጤው ሀገራት ከቀሪው የአፍሪካ አህጉር ጋር የሚኖራቸውን የኢኮኖሚ ትስስር የሚያሳልጥ ስትራቴጂካዊ መድረክ እንድትሆን እንደሚያስችላት ገልጸዋል። እየተከናወኑ ያሉ የኢንዱስትሪና የግብርና ልማት ሥራዎችም ለሀገራቱ የምግብ ዋስትና እና የኢንቨስትመንት ፍላጎቶች ተስማሚ ምላሽ መስጠት የሚያስችሉ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ተመራማሪው ይህም ኢትዮጵያን አጠቃላይ አህጉራዊውን የንግድና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ የሚያስተስስር ቁልፍ ማዕከል እንደሚያደርጋት አስታውቀዋል።
በጅማ ዞን በመኸር እርሻው 930 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር ተሸፍኖ እየለማ ነው
Aug 1, 2026 162
ጅማ፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ በጅማ ዞን በመኸር እርሻው 930 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር ተሸፍኖ እየለማ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ ቲጃኒ ተማም ለኢዜአ እንደገለጹት በዞኑ በ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት ለሰብል ምርትና ምርታማነት እድገት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በመኸር እርሻው 883 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ዘር በመሸፈን 36 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለማግኘት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ተናግረዋል። እስካሁን በተደረገ ጥረት ከእቅድ በላይ 930 ሺህ ሄክታር መሬት ታርሶ በበቆሎ፣ በጤፍ፣ በሩዝ እና በሌሎች ሰብሎች ዘር ኘሸፈኑን ገልጸዋል። በዘር ከተሸፈነው ውስጥ 200ሺህ ሄክታሩ በበቆሎ ዘር መሸፈኑን ጠቁመው ቀድሞ የተዘራ በመሆኑም አሁን ላይ በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ተናግርዋል። በምርት ወቅቱ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሰጠው ትኩረት አብዛኛው ሰብል በኩታ ገጠም የተዘራ መሆኑን አመልክተዋል። በዞኑ ከሚገኙ የግብርና ግብዓት ማዕከላትና ዩኒየኖች ጋር በመቀናጀትም የግብርና ግብዓቶችን በተሳካ መልኩ ማሰራጨት መቻሉንና ለአርሶ አደሩ እየተደረገ ያለው የክትትልና ሙያዊ ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቀዋል። በዞኑ ሊሙ ኮሳ ወረዳ በግብርና ልማት ከተሰማሩ ወጣቶች መካከል ሚልኮ ሙዲን ዓምና በቆሎን ከሌሎች የአካባቢው ወጣቶችና አርሶ አደሮች ጋር በክላስተር በማልማት የተሻለ ምርት ማግኘቱን አስታውሷል። በዘንድሮ ምርት ዘመንም ቀደም ብሎ የመሬት ዝግጅት በማድረግና አስፈላጊውን የግብርና ግብዓት በመጠቀም የዘራውን በቆሎ እየተንከባከበ መሆኑን ተናግሯል። ሌላው የወረዳው አርሶ አደር ጌታቸው አሊ በበኩላቸው ዘንድሮ በቆሎን በስፋት መዝራታቸውንና የበቆሎ ምርጥ ዘር በወቅቱ በማግኘታቸው የዘር ስራውን በወቅቱ ለማከናወን ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው አስረድተዋል።
በሲዳማ ክልል በመኸር እርሻ ከ169 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይለማል
Aug 1, 2026 154
ሀዋሳ ፤ ሐምሌ 25/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በተያዘው የመኸር እርሻ ከ169 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአዝርዕት፣ በጥራጥሬና በስራስር ሰብሎች እንደሚለማ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ እንደገለጹት፤ በሲዳማ ክልል በተያዘው የመኸር እርሻ ከ169 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በአዝርዕት፣ በጥራጥሬና በስራስር ሰብሎች ይለማል። ኃላፊው አክለውም መኸር አብቃይ ለሆኑ ወረዳዎች 183 ሺህ 410 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያና 47 ሺህ 458 ኩንታል ምርጥ ዘር መሰራጨቱን ገልጸዋል። ዘንድሮ በዘር ከሚሸፈነው ማሳ በጥራጥሬ፣ በብርዕና በሌሎች ዋና ዋና ሰብሎች 123 ሺህ ሄክታር መሬት እንደሚለማና ቀሪው በድንች፣ በስኳር ድንችና ሌሎች የስራ ስር ሰብሎች እንደሚለማ ገልጸዋል። አርሶ አደሩ ማሳውን ለዘር እያዘጋጀ እንደሚገኝና በአንዳንድ ወረዳዎች የዘር መዝራት ስራ እንደተጀመረ ጠቁመዋል። በበልግ እርሻ በዝናብ መቆራረጥ ምክንያት የጠፋ ሰብልን ለማካካስ ዘር እንደቀረበላቸውና በመኸር እርሻ ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን እንዲያለሙ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ የደራራ ወረዳ አርሶ አደር ተሰማ ተስፋዬ፣ በበልግ ወቅት በበቆሎ ያለማነውን የደረሰ ሰብል በማንሳት ለመኸር እርሻ ቦሎቄና የስራ ስር ሰብል ለማልማት ዝግጅት እያደረግን ነው ብለዋል። ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎች ዘር እንደቀረበላቸውና የግብርና ባለሙያዎች በቅርበት እገዛ እያደረጉላቸው መሆኑንም አርሶ አደሩ ገልጸዋል። አርሶ አደር ታዲዮስ መልካሙ በበኩላቸው በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ በመታገዝ በመኸር የሚያለሙትን ማሳ እያዘጋጁ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በበልግ እርሻ በቆሎ በኩታ ገጠም እንዳለሙ ያነሱት አርሶ አደሩ የመኸሩንም በዚሁ የእርሻ ስነ-ዘዴ እንደሚያለሙም ገልጸዋል። በክልሉ በመኸር እርሻ ከ430 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች እንደሚሳተፉና ከሚለማው 169 ሺህ ሄክታር ማሳ ከ15 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚሰበሰብ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ አስታውቋል።
የኢትዮጵያን ህልውና አስተማማኝ ለማድረግ በተደመረ መንገድ ወደ ብልጽግና መጓዝ ብቸኛው አማራጭ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 31, 2026 504
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 24/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ህልውና አስተማማኝ ለማድረግ በተደመረ መንገድ ወደ ብልጽግና መጓዝ ብቸኛው አማራጭ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን (አሚኮ) ጋር ቆይታ አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቆይታቸው፤ ከለውጡ ማግስት ጀምሮ ኢትዮጵያን አጽንቶ ማስቀጠል እና መገንባት ላይ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ሰፋፊ ውይይቶች መደረጋቸውን አመልክተዋል። ይህ ውይይት ወደ ባለድርሻ አካላት ከመምጣቱ በፊት በመንግስት ውስጥም ሰፊ ውይይቶች ይደረጉ እንደነበር አስታውሰዋል። በእነዚህ ውይይቶችም ሀገሪቱን ለማሳደግ ባሉ አቅሞች እና ኢትዮጵያን በመገንባት ሂደት ላይ በትብብር መስራት በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ዙሪያ ሰፊ ምክክር መደረጉን አውስተዋል። እነዚህ የተደረጉት ውይይቶች የጠራ አካሄድ እና መንገድን ለመከተል ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። በተጨማሪም በኢትዮጵያ በተለያዩ አካባቢዎች የተካሄዱ ህዝባዊ ውይይቶች የህዝብን የልብ ትርታ ለማዳመጥና ፍላጎቱን በግልጽ ለማወቅ ማስቻላቸውን ጠቅሰዋል። የአማራ ክልልን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የተደረጉት ውይይቶች የኢትዮጵያውያን ፍላጎት የተቀራረበ መሆኑን ማየት አስችለዋል ነው ያሉት። የሪፎርሙ ዋና አካል የሆኑት የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ስብራቶች በውይይቶቹ ውስጥ ጎልተው መታየታቸውን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ እነዚህን ስብራቶች መጠገንም የሚያስችሉ ሀሳቦች መቅረባቸውን ገልጸዋል። ከኢኮኖሚው ወይም ከፖለቲካው አንዱን ብቻ በመክፈት ዘላቂ መፍትሄ እንደማይመጣ አመልክተው፤ ሁለቱንም ክፍት በማድረግ የምንመኛት ኢትዮጵያን መገንባት እንደምንችል እሳቤ ለመቅረጽ ውይይቶቹ ወሳኝ ሚና መጫወታቸውን ተናግረዋል። በዚህም ብቸኛው መንገድ በተደመረ መንገድ ወደ ብልጽግና መጓዝ እንደሆነና የኢትዮጵያን ህልውና አስተማማኝ በሆነ ሁኔታ ለማረጋገጥ መደመርና ማበልፀግ እንደሚገባ ወደሚያሳየው መንግስታዊ ንድፍ መገባቱን አስረድተዋል።
በሰሜን ጎጃም ዞን ለመኸር ወቅት ከታቀደው ከ93 በመቶ በላይ የሚሆነው የእርሻ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Jul 31, 2026 393
ባህር ዳር ፤ሐምሌ 24/2018 (ኢዜአ) ፦ በሰሜን ጎጃም ዞን ለዘንድሮው የመኸር ወቅት ከታቀደው ከ93 በመቶ በላይ የሚሆነው የእርሻ መሬት በዘር መሸፈኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ምክትል ኃላፊ አቶ መልካሙ አለኸኝ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው የምርት ዘመን የሚታረሰውን መሬት በሙሉ በዘር በመሸፈን በምግብ ራስን ከመቻል አልፎ ለገበያ የሚሆን ምርት ለማምረት እየተሰራ ይገኛል። ለመኸር ምርት ዘመኑ ከ332 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከ17 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዶ እየተሰራ ሲሆን፣ እስካሁን ከ93 በመቶ በላይ የሚሆነውን መሬት በዘር መሸፈን ተችሏል ብለዋል። የተጠቀሰውን መሬት በበቆሎ፣ በጤፍ፣ በሩዝ፣ በአኩሪ አተርና በቦሎቄ ሰብሎች በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ መዝራት መቻሉን ተናግረዋል። ምርታማነትን ለማሳደግም ለዞኑ ከቀረበው ከ780 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ውስጥ 83 በመቶ የሚሆነው እንዲሁም 38 ሺህ 700 ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር በማሰራጨት ጥቅም ላይ እንዲውል መደረጉን አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅትም ቀደም ብሎ የተዘራው ሰብል ቡቃያ በጥሩ ቁመና ላይ የሚገኝ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ አርሶ አደሩ የአረም፣ የኩትኳቶና የተባይ አሰሳ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ዝናብ ዘግይቶ በጣለባቸው አካባቢዎችም ያልተዘሩ ማሳዎችን ፈጥነው በሚደርሱ ሰብሎች ለመሸፈን የዘርፉ አመራርና ባለሙያ አርሶ አደሩን እየደገፈ ይገኛል ብለዋል። በዞኑ ሰሜን ሜጫ ወረዳ እንጉቲ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ስሜነህ አበረ እንደገለጹት፤ የቀረበላቸውን ማዳበሪያ በመጠቀም በቆሎ፣ ዳጉሳና ጤፍ ዘርተዋል። የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ካሳሁን አበበ በበኩላቸው፤ በዘንድሮው የመኸር እርሻ ሁለት ሄክታር ማሳቸውን በበቆሎና በጤፍ ዘር ሸፍነዋል። በቂ ማዳበሪያ በወቅቱ በማግኘታቸው ዝናብ እንደጣለ ፈጥነው ለመዝራት እንዳስቻላቸው ጠቁመው፤ አሁን ላይ ቡቃያው ጥሩ በመሆኑ የተሻለ ምርት እንደሚያገኙ ተስፋ አድርገው እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።
በክልሉ በማዕድን ዘርፍ ልማት ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት ለመተካት ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 31, 2026 410
አርባምንጭ፣ ሐምሌ 24/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በማዕድን ዘርፍ ልማት የግል ባለሃብቶችን ተሳትፎ በማሳደግ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት ለመተካት ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ማዕድን ባለስልጣን ገለጸ፡፡ መንግስት ለሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትኩረት ከሰጠባቸው አምስት ዘርፎች መካከል የማዕድን ዘርፉ አንዱ ነው። በማዕድን ልማቱም የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ በማሳደግ የሀገር ውስጥ ምርትን በራስ አቅም ለመሸፈን፣ ለኢኮኖሚው የሚያበረክተውን ፋይዳ ለማሳደግና የሥራ ዕድል ለመፍጠር ያለው አበርክቶ የጎላ ነው። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ሔለን ዮሐንስ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክልሉ በማዕድን ዘርፍ ልማት የግል ባለሃብቶችን ተሳትፎ በማሳደግ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት ለመተካት ትኩረት ተሰጥቷል። በክልሉ ጋሞ ዞን ቦረዳ ወረዳ የተገነባው የ"ዮ ሆልዲንግስ" የድንጋይ ከሰል ፋብሪካ መንግስት ለሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያና ለግሉ ዘርፍ ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ያለውን ቁርጠኝነት በተግባር ያሳየበት መሆኑን ገልጸዋል። ፋብሪካው ከውጭ የሚገባውን የድንጋይ ከሰል ምርት በመተካትና በስራ ዕድል ፈጠራ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ፋብሪካው የድንጋይ ከሰል በማምረት ለኢንዱስትሪዎች ግብዓት ከውጭ የሚገባውን በመተካት የውጭ ምንዛሬን ከማዳን ባለፈ፣ ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። የዮ ሆልዲንግስ ፋብሪካ ጄኔራል ማናጀር ኤፍሬም ታደሰ ፋብሪካው በሰዓት 220 ቶን፣ በዓመት ደግሞ 1 ነጥብ 3 ሚሊየን ቶን የድንጋይ ከሰል የማምረት አቅም እንዳለው ገልጸዋል። ድርጅቱ ሀገሪቱ ያላትን የተፈጥሮ ጸጋ በማበልጸግ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ከማሟላት ባለፈ፣ ወደ ውጭ ሀገር በመላክ የውጭ ምንዛሬ ለማስገኘት አቅዶ እየሰራ መሆኑን አስረድተዋል። ፋብሪካው የውጭ ምንዛሬ ከማዳን ባለፈ ለዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉንም ተናግረዋል። በተጨማሪም ምርቱ በጥራቱ ከውጭ ከሚገባው ጋር የሚስተካከልና በዋጋውም ተመጣጣኝ መሆኑን አመልክተዋል።
በኡማ ወንዝ ላይ የተገነባው ድልድይ ለዘመናት ከቆየንበት ችግርና እንግልት ታድጎናል- የአካባቢው ነዋሪዎች
Jul 31, 2026 366
ቦንጋ ፤ ሀምሌ 24 /2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ኮንታ ዞን ኡማ ወንዝ ላይ የተገነባው ድልድይ ለዘመናት ከቆየንበት ችግርና እንግልት ታድጎናል ሲሉ የአካባቢው ነዋሪዎች ተናገሩ። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ሰው ተኮር ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት ገንብቶ በማጠናቀቅ የዜጎችን ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራ ተጠናክሮ ቀጥሏል። በተለይም የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን በመገንባት የወረዳና ቀበሌዎች ማህበራዊ ትስስር እንዲጠናከርና የግብይት ሰንሰለትም እንዲቀላጠፍ እየተደረገ ይገኛል። ከሰሞኑን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ኮንታ ዞን በአመያ ዙሪያ ወረዳ በኡማ ወንዝ ላይ የተገነባው ድልድይ የአካባቢውን ነዋሪዎች የዘመናት ችግር ያቃለለና ለመሰረተ ልማት ጥያቄያቸው ምላሽ የሰጠ መሆኑ ተገልጿል። ከአካባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ ገዛሃኝ ገንባራ እና አቶ ገረመው ባረንጎ፤ የኦማ ወንዝ ድልድይ መገንባት የአካባቢውን ነዋሪዎች የዘመናት ችግር የፈታ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይ በክረምት ወቅት ወንዙን ተሻግሮ መሄድ አስቸጋሪ ስለነበር በተለይም ነፍሰ ጡሮች ወደ ህክምና ለመሄድ፤ አቅመ ደካሞችም ለመሻገር አይችሉም ነበር ብለዋል። በዚህም ምክንያት በርካታ ችግሮች አልፈዋል ያሉት አስተያየት ሰጪዎቹ የድልድዩ መገንባት ዘርፈ ብዙ መፍትሄዎችን ያመጣ መሆኑን ገልጸዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ የባቄ ዚጋ ቀበሌ ነዋሪዋ ወ/ሮ አንቴቴ ዱካ፤ የወንዙ መሸጋገሪያ ድልድይ አለመኖሩ ለህክምናም ይሁን ለገበያ መሸጋገር አንችልም ነበር ብለዋል። በመሆኑም አሁን ላይ ደረጃውን የጠበቀ ትልቅ ድልድይ በመግባቱ ለዘመናት የነበረብንን ችግር የፈታና ከሌሎች አካባቢዎች ጋር በቀላሉ መገናኘት አስችሎናል ሲሉ ተናግረዋል። የክልሉ መንገዶች ባለሥልጣን ዋና ስራአስኪያጅ ኢንጂነር አብድዩ መኮንን፤ የድልድዩ መገንባት የአካባቢውን ማህበረሰብ ችግር ከመፍታት ባለፈ በርካታ አካባቢዎችን ማስተሳሰርና ማገናኘት ያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ በክልሉ ከኡማ ወንዝ ድልድይ ግንባታ በተጨማሪ የ177 ኪሎ ሜትር መንገድ ግንባታ መጠናቀቁን አንስተው የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች ተጠናክረሮ ይቀጥላል ብለዋል። በቀጣይም ያሉ አቅሞችን አቀናጅቶ ወደ ተግባር በመግባት የተጀመሩ ፕሮጀክቶችን በፍጥነት የማጠናቀቅና ሌሎችንም የመገንባት ስራ ትኩረት ተሰጥቶታል ሲሉም ተናግረዋል።
በክልሉ በግብርናው ዘርፍ ያሉትን ፀጋዎች ለይቶ ለማልማት የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያመጡ ነው
Jul 31, 2026 329
ዱራሜ ፤ ሐምሌ 24/2018ዓ.ም (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በግብርናው ዘርፍ ያሉትን ፀጋዎች ለይቶ ለማልማት የተከናወኑ ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። ቢሮው "በተቀናጀ ግብርና የቤተሰብ ብልፅግና" በሚል መሪ ሃሳብ ከቢሮው ከፍተኛ አመራሮችና ከግብርና ዘርፍ ባለሙያዎች ጋር ያዘጋጀው የውይይት መድረክ በዱራሜ ከተማ እየተካሄደ ነው። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የግብርናና ገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር እንዳሉት ፤በክልሉ በግብርናው ዘርፍ ያሉትን ፀጋዎች ለይቶ የማልማት ስራዎች ውጤት እያመጡ ነው። መንግስት የውስጥ አቅምን በመጠቀም ከሀገር አልፎ ለውጪ ገበያ የሚቀርብ ምርት እንዲመረት እየፈጠረ ባለዉ ምቹ ሁኔታ ዘርፈ ብዙ ስኬቶች እየተመዘገቡ መሆኑንም ነው የተናገሩት። በግብርናው ዘርፍ ክልሉ ያለውን የመልማት አቅም መሰረት ያደረገ ጥናት በማዘጋጀት በኢኮኖሚ ራሱን የቻለ እና ከድህነት የተላቀቀ ማህበረሰብን ለመፍጠር ዘርፈ ብዙ ተግባራት ተከናውነዋል ነው ያሉት፡፡ በመደበኛ ግብርና ስራ ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ፣ በንብ ማነብ፣ በእንሰሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ዘርፍ ያሉ አቅሞችን ለይቶ መጠቀም በመቻሉ ምርትና ምርታማነት ማሳደግ አስችሏል ብለዋል፡፡ በዚህም የምግብ ዋስትናን በቤተሰብ ደረጃ ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያና ለኢንዱስትሪ የሚተርፍ ምርት በማምረት የአርሶ አደሩም ተጠቃሚነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ጠቁመዋል። በቢሮው የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም ማናጀር አቶ ከድር መሀመድ በበኩላቸው፤ በክልሉ በግብርናው ዘርፍ ያለውን የመልማት አቅም ታሳቢ ያደረገ እና በጥናት ላይ የተመሰረተ እቅድ ተዘጋጅቶ እየተተገበረ እንደሆነም አብራርተዋል። ከመደበኛ የግብርና ስራዉ በተጨማሪ ውስን መሬትን በመጠቀም በአረንጓዴ አሻራ ፣ በንብ ማነብ ፣ በዶሮ እርባታ ፣ አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ በሌሎች ዘርፎች ምርታማነት እንዲጨምር የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚ በማሻሻልና በምግብ ራስን በመቻል ከተረጂነት ለመውጣት እየተደረገ ባለው ጥረት ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን ነው የተናገሩት፡፡
በምዕራብ ወለጋ ዞን ከ81 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ሰብል እየለማ ነው
Jul 31, 2026 328
ጊምቢ፣ሐምሌ 24/2018(ኢዜአ)፦በምዕራብ ወለጋ ዞን ከ81 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ሰብል በመልማት ላይ እንደሚገኝ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። ምዕራብ ወለጋ ለበቆሎ ምርት ተስማሚ የሆነ የአየር ንብረት፣ ለም አፈር እና በቂ የዝናብ ስርጭት ያለው አካባቢ ነው። የበቆሎ ሰብል ለአካባቢው አርሶ አደሮች ዋና የምግብ ምንጭ ከመሆኑ ባሻገር ለገበያ በመቅረብ ከፍተኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የሚፈጥር ሰብል ነው። ይህንን ሰፊ መሬት በበቆሎ ለመሸፈን አስቀድሞ የመሬት ዝግጅት ከተከናወነ በኋላ ምርጥ ዘር፣ ማዳበሪያ እና የፀረ-ተባይ መድሃኒቶች ለአርሶ አደሩ ቀርቦ ከ81 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ሰብል መልማቱ ነው የተገለጸው። የግብርና ኤክስቴንሽን ባለሙያዎችም የምርት ሂደቱን እና የሰብል እንክብካቤውን በቅርበት እየተከታተሉ መሆናቸው እንዲሁ። የምዕራብ ወለጋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ሀላፊ አቶ ፈይሣ ሀምቢሳ እንደገለጹት፥ የበቆሎ ምርታማነትን ለማሳደግ አርሶ አደሮች በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ እንዲያርሱ እየተደረገ ነው። አክለውም፣ ለዘመኑ እርሻ የሚያስፈልጉ ልዩ ልዩ የግብርና ግብዓቶች በወቅቱ ለአርሶ አደሩ እንዲቀርቡና ጥቅም ላይ እንዲውሉ መደረጉን አመልክተዋል። በተለይም የዘንድሮ የአየር ሁኔታ ለቦቆሎ ሰብል አመቺ በመሆኑ የተሻለ ምርት እንደሚጠበቅም ገልጸዋል። በዚህም በበቆሎ ሰብል እየለማ ካለው 81 ሺህ 244 ሄክታር መሬት ከ3 ሚሊዮን 845 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ ኃላፊው አመልክተዋል። በዞኑ በበቆሎ ሰብል ልማት ላይ ከተሰማሩት አርሶ አደሮች መካከል የቤጊ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አቶ አብዱላሂ ሙሐመድ አንዱ ናቸው። አርሶ አደሩ ከግብርና ባለሙያዎች በሚያገኙት ሙያዊ ምክር እና ባላቸው የቆየ ልምድ በመታገዝ፣ አንድ ሄክታር መሬታቸውን በበቆሎ ሰብል ሸፍነው አስፈላጊውን እንክብካቤ በማድረግ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም ከአንድ ሄክታር ከ30 ኩንታል ያልበለጠ ምርት ያገኙ እንደነበር ያስታወሱት አርሶ አደሩ፣ ዘንድሮ ግን እስከ 40 ኩንታል የበቆሎ ምርት ለማግኘት የሚያስችሉ አስፈላጊ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን እየተጠቀሙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በየዓመቱ በስፋት የበቆሎ ሰብል እንደሚያለሙ የተናገሩት ደግሞ ሌላኛው አርሶ አደር አቶ ደቤላ ዲንሳ ናቸው። አርሶ አደሩ አክለውም፣ በዘንድሮው የምርት ዘመን በአንድ ሄክታር መሬታቸው ላይ በኩታ ገጠም የአስተራረስ ዘዴ የበቆሎ ሰብል በማልማት ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የዘንድሮው የአየር ሁኔታ ለምርት ሂደቱ አመቺ በመሆኑ፣ የተሻለ ምርት ለማግኘት ሙሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመው መዝራታቸውን አርሶ አደሩ ገልጸዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል
Jul 30, 2026 773
አምቦ ፤ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ):- በምዕራብ ሸዋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በዞኑ አደአ በርጋ ወረዳ ግንባታቸው የተጠናቀቁ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ተደርገዋል፡፡ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ በምረቃ ስርዓቱ ላይ እንደገለጹት፣ በዞኑ በርካታ የልማት ስራዎችን በማከናወን የህዝቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው። በ2018 በጀት ዓመት ከ5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ በሚሆን ወጪ በዞኑ በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች የተገነቡ 585 ፕሮጀክቶች ተጠናቀቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን በማሳያነት አንስተዋል። "የማንጨርሰውን ፕሮጀክት አንጀምርም" ብለን ለህዝባችን ቃል በገባነው መሰረት ሁሉንም ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በማብቃታችን ታላቅ ደስታ ይሰማናል በማለትም ተናግረዋል፡፡ በዞኑ የአደኣ በርጋ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ከበደ በቀለ በበኩላቸው፤ በወረዳው በመንግሥት በጀትና በሕብረተሰቡ ተሳትፎ ከ 274 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነቡ 33 የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን አስታውቀዋል። ዛሬ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ከሆኑት ፕሮጀክቶች መካከል፣ የቅድመ መደበኛና አንጀኛ ደረጃ "ኦልማ አዳ" ትምህርት በቶች፣ ሞዴል የህዝብ መድሃኒት ቤት፣ የከብቶች ማድለቢያና ለዶሮ እርባታ የሚሆኑ ሼዶች እና የኢንጭኒ ከተማ ኮሪደር ልማት ይገኙበታል ብለዋል። ፕሮጀክቶቹ የሕዝቡን የልማት ጥያቄ ከመመለስና የመልካም አስተዳደር ችግርን ከመፍታት ባለፈ ለዜጎች የስራ እድል እንደፈጠሩላቸውም ገልጸዋል። በወረዳው ባለፉት ጥቂት ዓመታት የሰላም እጦት ችግር እንደነበረና አሁን ላይ ህብረተሰቡ ከመንግሥት ፀጥታ ሃይሎች ጋር ተቀናጅቶ በመስራት በተገኘው ሰላም የህዝቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ የሚችሉ የልማት ፕሮጀክቶችን ለአገልግሎት ማብቃት መቻሉን ጠቁመዋል። በምረቃው ላይ የተገኙት የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው የልማት ፕሮጀክቶቹ ግንባታ የረጅም ጊዜ ጥያቄያቸው መልስ ያገኘበት በመሆኑ መደሰታቸውን በመግለጽ፤ አሁን ያገኙትን ሰላም በማፅናት የተመረቁ ፕሮጀክቶችን እየተንከባከቡ ለመጪው ትውልድ እደሚያሳልፉ ተናግረዋል። ከአከባቢው ነዋሪዎች መካከል አባ ገዳ ግርማ ዱጉማ፤ ፕሮጀክቶቹ የረጂም ጊዜ ጥያቄያቸው የተመለሰበት ስለሆነ ጠብቀው ለተተኪው ትውልድ ለማስተላለፍ ሃላፊነታቸውን የሚወጡ መሆኑን ገልጸዋል። ሌላው የወረዳው ነዋሪ ወይዘሮ ተዋበች በቀለ በበኩላቸው በአካባቢያቸው የተሰራው ሞዴል የህዝብ መድሃኒት ቤት የነበረባቸውን የጤና አገልግሎት ችግር ለመፍታት የሚያስችል በመሆኑ ደስታቸውን ገልጸዋል።
በጅማ ዞን የተገነቡ ፕሮጀክቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ አድርገዋል
Jul 30, 2026 816
ጅማ፤ ሀምሌ 23/2018 (ኢዜአ) ፡-በጅማ ዞን በመንግስትና በህዝብ ተሳትፎ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ ማድረጋቸውን የጅማ ዞን አስተዳዳሪ ቲጃኒ ናስር ገለጹ። በጅማ ዞን ሰቃ ጨቆርሳ ወረዳ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። ከፕሮጀክቶቹ መካከል የግብርና ግብዓት ማከማቻ፣ የመንገድ፣ ድልድይ ፣የሁለተኛ ትውልድ የጤና ኬላ፣ የገበያ ማዕከል እና የወረዳው አስተዳደር ህንፃን ጨምሮ ሌሎችም ይገኙበታል። የጅማ ዞን አስተዳዳሪ ቲጃኒ ናስር በወቅቱ እንዳሉት የህብረተሰቡን የመሠረተ ልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ፕሮጀክቶች በፍጥነትና በጥራት ተገንብተው እንዲጠናቀቁ እየተደረገ ነው ። በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በመንግስት እና በህዝብ ተሳትፎ የተገነቡ ፕሮጀክቶች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ አድርገዋል ብለዋል ። በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት አመት በ5 ነጥብ 1 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ ከ1 ሺህ 876 በላይ ፕሮጀክቶች መገንባታቸውን ተናግረዋል ። ፕሮጀክቶቹ ለህዝብ ለጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የሰቃ ጨቆርሳ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አብዱልከሪም አባራያ በበኩላቸው በወረዳው በበጀት ዓመቱ ከ800 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ግንባታቸው ከተጀመሩ 33 ፕሮጀክቶች ውስጥ 23ቱ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ተደርገዋል ብለዋል። ቀሪዎቹም በአጭር ጊዜ ውስጥ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚደረጉ አመላክተዋል ። የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ እየተደረገ ያለው የመሠረተ ልማት ግንባታ የሚበረታታ ነው ያሉት ደግሞ በጅማ ዞን ሰቃ ጨቆርሳ ወረዳ ነዋሪ አቶ መሀመድ ዘይን ተማም ናቸው። አቶ አበዱላሂ አባ ጀበል በበኩላቸው በወረዳው ዶዩ ቃጨማ ቀበሌ የተገነባው የግብዓት ማቆያ እና ማከማቻ ከዚህ ቀደም የግብርና ግብአቶችን ለማግኘት ወደ አጎራባች ወረዳዎች በመጓዝ የሚባክንን ግዜና ገንዘብ እንደቆጠበላቸው ተናግረዋል።
በ2018 በጀት ዓመት በመንግሥት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ከ597 ቢሊየን ብር በላይ ግዥ ተፈጽሟል
Jul 30, 2026 904
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በመንግሥት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ከ597 ቢሊየን ብር በላይ የተጠናቀቀ ግዥ መፈጸሙን የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን ገለጸ። ባለሥልጣኑ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት ግዥና ንብረት አስተዳደር አፈጻጸምና የ2019 ዕቅድ ላይ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ጋር ምክክር እያደረገ ይገኛል። በመርሃ ግብሩ የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴን ጨምሮ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶችና የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር መሰረት መስቀሌ በዚህ ወቅት፤ ባለሥልጣኑ የመንግሥት ግዥ ሥርዓትን፣ የንብረት አስተዳደርንና አወጋገድ ሂደትን በኤሌክትሮኒክ ሥርዓት በማስተዳደር ለዲጂታል ኢትዮጵያ ሽግግር ገንቢ ሚና እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል። በ2018 በጀት ዓመት 172 የፌዴራል መሥሪያ ቤቶችና 196 ቅርንጫፍ ተቋማቶቻቸው የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትን መጠቀማቸውን ገልጸዋል። በዚህ ሥርዓት ተመዝግበው ምርትና አገልግሎት የሚያቀርቡ ተቋማት ቁጥርም ከ135 ሺህ በላይ መድረሱን ጠቁመዋል። የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓቱ በየጊዜው ማሻሻያ እየተደረገለት ለአጠቃቀም ምቹ፣ ግልጽነትና ተጠያቂነትን የሚያሰፍን እየሆነ መምጣቱንም ተናግረዋል። በዚህም በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመት በመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓት ከ597 ቢሊየን ብር በላይ ግዥ መፈጸሙን አስታውቀዋል። የግዥ ሥርዓቱ ከፌዴራል ተቋማት ባለፈ በኦሮሚያ ክልልና በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተግባራዊ መደረጉን አስረድተዋል። በሌሎች ክልሎችም የሥርዓቱን መሠረተ ልማት ለማስፋፋት በስልጠናና በአቅም ግንባታ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። ባለሥልጣኑ ከኤሌክትሮኒክ ግዥ ባሻገር የተሽከርካሪዎችን እንቅስቃሴና የነዳጅ አጠቃቀም መቆጣጠር የሚያስችል ''e-Fleet Management'' ሥርዓት ወደ ሥራ ማስገባቱንም ገልጸዋል። በዚህም 139 ተቋማት ሥርዓቱን ለመጠቀም መግባታቸውንና 69 ተቋማት ከ7 ሺህ በላይ ተሽከርካሪዎችን መረጃ መመዝገባቸውን ጠቁመዋል። በ2019 በጀት ዓመትም ሁሉም ባለበጀት መሥሪያ ቤቶች ወደ ሥርዓቱ እንዲገቡ ክትትል እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። በ2018 በጀት ዓመት የተመዘገቡ ውጤቶች የአገልግሎት አሰጣጡን ማቀላጠፍና የቁጥጥር ሥርዓቱን ማጠናከር የሚያስችል የዲጂታል ሽግግር እየተፈጠረ መሆኑን ያሳያሉ ብለዋል።
በዞኑ የማር ምርት አቅርቦትና ተጠቃሚነት አድጓል
Jul 30, 2026 912
መቱ ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦ በዞኑ የማር ምርት ቴክኖሎጂ፣ አቅርቦትና ተጠቃሚነት ማደጉን የኢሊባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አወል መሐመድ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤ባለፉት አምስት ዓመታት ለማር ምርት በተሰጠው ትኩረት በዘርፉ ለውጥ ለማምጣት ተችሏል። በዋናነትም ዘመናዊ ቀፎና ለስራው የሚያስፈልጉ ተያያዥ ቴክኖሎጂዎችን በስፋት በማዳረስ ዘርፉን ለማሳደግ በተደረገው ጥረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልፀዋል። ይህን ተከትሎም ከአምስት ዓመታት በፊት በዞኑ ከ5 ሺ ቶን የማይበልጥ የነበረው ዓመታዊ የማር ምርት መጠንን ወደ 20 ሺ ቶን ከፍ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። በመስኩ በቀፎ ማምረት ስራ ተደራጅተው የተሰማሩትን ጨምሮ ለአርሶ አደሮችና በማር ንግድ ለተሰማሩ ዜጎች ሰፊ የስራ ዕድል መከፈቱንም ተናግረዋል። በዞኑ በቾ ወረዳ ከ8 ሺ በላይ አርሶ አደሮችና ማሕበራት በንብ ማነብና የማር ምርት ተሰማርተው እንደሚገኙ የገለጹት ደግሞ የወረዳው ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ዲቤሳ ናቸው። ጽህፈት ቤቱ ለዘመናዊ ቀፎ አቅርቦት በሰጠው ትኩረትም ከ50 ሺህ በላይ ቀፎዎችን ለማሕበራትና አርሶ አደሮች ማቅረብ መቻሉን ገልፀዋል። በወረዳው የማር ምርት ልማት ላይ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል ወይዘሮ አይናለም ጌታቸው፤ በ12 ቀፎዎች የጀመሩትን የማር ምርት ወደ ሃምሳ ቀፎ ማሳደጋቸውን ነው የሚናገሩት። በማር ምርቱ የቤተሰብ ፍጆታን ከመሸፈን ባለፈ በዓመት እስከ ሶስት መቶ ኪሎ ግራም ለገበያ እንደሚያቀርቡ ተናግረዋል። ወጣት ሻቡ አብዱራህማን እና ጓደኞቹ በበኩላቸው፤ በማሕበር ተደራጅተው በማር ምርት በመሰማራት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። በመስኩ ጠንክረው በመስራት ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ የስራ እድል ለመፍጠር ጠንክረው እየሰሩ መሆኑንም ገልጸዋል። በኢሉባቦር ዞን በአጠቃላይ ከ70 ሺ በላይ አርሶ አደሮች በንብ ማነብና በማር ምርት ልማት ተሰማርተዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓት ውጤታማነትን አሻሽሏል
Jul 30, 2026 927
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 23/2018(ኢዜአ)፦ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ስርዓትንና የወጪ ውጤታማነትን ማሻሻሉን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገለጹ። የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት ግዥና ንብረት አፈጻጸምና የ2019 ዕቅድን በተመለከተ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶችና የሀብት አስተዳደር ኃላፊዎች ጋር ውይይት አድርጓል። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የመንግሥት ግዥና ንብረት አስተዳደር ሥርዓት ለኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለፊስካል መረጋጋት፣ ለመንግሥት ወጪ ቅልጥፍና፣ ለግልጽነትና ተጠያቂነት መጠናከር የጎላ ስትራቴጂካዊ ሚና አለው። የመንግሥት ግዥ የመንግሥት ፖሊሲ ወደ ተግባር የሚቀየርበት፣ የሕዝብ ሀብት በኃላፊነት የሚተዳደርበት፣ የአገልግሎት ጥራትን የሚያሻሽልና ሀገራዊ ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን የሚደግፍ መሆኑን ገልጸዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት የመንግሥት ኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትንና የወጪ ውጤታማነትን ማሻሻል አስችሏል ብለዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የመንግሥት የኤሌክትሮኒክ ግዥን በማስፋት፣ የግዥ ዝመናን በማጠናከር፣ ሕጎችና አሠራሮችን በማዘመን አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፤ ተቋማዊ አቅምን ከማጠናከር ባለፈ በመንግሥት ወጪ ላይ ግልጽነትና ተጠያቂነትን ያጠናከሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። መንግሥት ለትምህርት፣ ለጤና፣ ለግብርና፣ ለውኃ፣ ለመሠረተ ልማት፣ ለዲጂታል ልማትና መሰል ዘርፎች የሚመድበው በጀት በመንግሥት ግዥ ወደ ተግባር፤ የልማት ፖሊሲ ወደ ውጤት የሚቀየርበት መሆኑንም ተናግረዋል። የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን በኤሌክትሮኒክ ግዥ፣ በዲጂታላይዜሽንና በአሠራር ማሻሻያዎች ያስመዘገባቸው ውጤቶች በመንግሥት ወጪዎች ላይ ያለውን ግልጽነትና ተጠያቂነት የሚያጠናክሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በመንግሥት ግዥ ላይ የሚሻሻለው እያንዳንዱ ሂደት በዜጎች ሕይወት ላይ ተጨባጭ ውጤት የሚያመጣ መሆን አለበት ሲሉም አስገንዝበዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርሙ ግብ የፊስካል ሥርዓትን ማጠናከር፣ የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ማሳደግና የመንግሥት ወጪን ውጤታማ ማድረግ መሆኑን ገልጸው፤ ለግቡ መሳካት የመንግሥት ግዥ ሥርዓቱን ቀልጣፋ፣ ግልጽና ተጠያቂነት የሰፈነበት ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። በ2019 በጀት ዓመት ሁሉም የፌዴራል ተቋማት የሚመሩበት መርህ ትክክለኛነት፣ ጥራትና ወቅታዊነት መሆኑን ያነሱት ሚኒስትሩ፣ የመንግሥት ግዥና ንብረት ባለሥልጣን የዲጂታል ሪፎርም የኢትዮጵያን የዲጂታል ሽግግር ይደግፋል ብለዋል። የዲጂታል ሽግግር አማራጭ ሳይሆን ግዴታ ነው ያሉት ሚኒስትሩ፣ በበጀት ዓመቱ ሁሉም የፌዴራል ተቋማት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ሥርዓትን በተሟላ ሁኔታ መጠቀም፣ የመንግሥትን ንብረት በዘመናዊ መንገድ ማስተዳደር እንዳለባቸውም ገልጸዋል። የመንግሥት ሀብት የሕዝብ አደራ መሆኑን ገልጸው፤ የሕዝብን አደራ በታማኝነት መጠበቅ የሁሉም የመንግሥት ተቋማት የመጀመሪያ ግዴታ ነው ብለዋል።