ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ወጣቶችን በክህሎትና በአመለካከት ብቁ በማድረግ በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ለውጥ ማምጣት ተችሏል
Aug 14, 2026 140
ሐዋሳ፤ ‎ነሐሴ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል ወጣቶችን በክህሎትና በአመለካከት ብቁ በማድረግ በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትርጉም ያለው ለውጥ ማምጣት መቻሉን የክልሉ ሥራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ፡፡ በኢትዮጵያ ኢንተርፕርነርሺፕ ልማት ኢንስቲትዩት ለወጣቶች ቀጣይነት ያለው የሥራ ዕድል ፈጠራ ፕሮግራም ''SEED'' በሲዳማ ክልል የሦስት ዓመት የሥራ አፈጻጸምና ቀጣይ አቅጣጫ ላይ የሚመክር መድረክ በሐዋሳ ከተማ ተካሄዷል፡፡   የሲዳማ ክልል ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሀገረጽዮን አበበ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ በክልሉ ወጣቶችን በክህሎትና በአመለካከት በማብቃት በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትርጉም ያለው ለውጥ ማምጣት ተችሏል፡፡ ከዚህ ቀደም የነበረው የሥራ ዕድል ፈጠራ ክህሎት መር ባለመሆኑ የተነሳ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ዜጎች ውጤታማ አለመሆን የዘርፉ ፈተና ሆኖ መቆየቱን አስታውሰዋል። ዘርፉ በዜጎች ክህሎትና አመለካከት ላይ የተመሠረተ እንዲሆን እንደ ሀገር አቅጣጫ ተይዞ መሥራት ከተጀመረ በኋላ፤ በተለይ ወጣቶች በተሻለ አቅምና ፍላጎት ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን ጠቁመዋል፡፡   በዚህም ውጤታማ የሆኑና ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች የሥራ ዕድል መፍጠር የቻሉ በርካታ ወጣቶችን ማፍራት እንደተቻለ ጠቅሰው፤ በዚህ ረገድ የባለድርሻ አካላት ቅንጅት ከፍተኛ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የቢሮው ምክትልና የሥራ ዕድል ፈጠራ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ከፍያለው ከበደ በበኩላቸው፤ አጋር አካላትን ከሥልጠና ተቋማት ጋር በማቀናጀት የክህሎት ክፍተቶችን የመሙላት እና ወደ ሥራ የሚገቡትን የማብቃት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡   ቅድሚያ ለክህሎትና አመለካከት በመስጠት የፋይናንስ፣ እንዲሁም የመሥሪያና የመሸጫ ቦታዎችን የማቅረብ ሥራ እየተሠራ መሆኑንም አክለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ኢንተርፕረነርሺፕ ልማት ኢንስቲቲዩት የሲዳማ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ፣ የደቡብ ኢትዮጵያና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልሎች አስተባባሪ አቶ ጌትነት ሳሙኤል፤ በኢንስቲትዩቱ የሚመራው የሥራ ዕድል ፈጠራ ፕሮግራም በአምስት ዓመታት ውስጥ ለ1 ሚሊዮን ወጣቶች ቀጣይነት ያለው የሥራ ዕድል የመፍጠር ዕቅድ አለው ብለዋል፡፡   ፕሮግራሙ ከተመረጡ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ጋር በመሆን የክህሎት ሥልጠና የመስጠት፣ እንዲሁም ከፋይናንስ ተቋማት ጋር በመቀናጀት የብድር አቅርቦት የማመቻቸት ሥራ እንደሚሠራ አስረድተዋል፡፡ በፕሮግራሙ በሲዳማ ክልል በሦስት ዓመታት ውስጥ ከ27 ሺህ በላይ ወጣቶች የክህሎት ሥልጠና ያገኙ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ19 ሺህ በላይ የሚሆኑት የሥራ ዕድል እንደተፈጠረላቸው አብራርተዋል፡፡ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጋር በመቀናጀትም ለኢንተርፕራይዞች ከ181 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር እንደተሰራጨ ጠቁመዋል፡፡   በፕሮግራሙ ድጋፍ ካገኙ ኢንተርፕራይዞች መካከል የጠይም ጋርመንት አባል የሆነችው ወጣት ቤርሳቤህ አለማየሁ እና የጃዋታ ጨርቃ ጨርቅ ማኅበር አባል የሆነችው ወጣት ራህመት ሁሴን፤ በፕሮግራሙ ባገኙት ሥልጠና ከዚህ ቀደም የነበረባቸውን የሂሳብ አያያዝና ሌሎች ክፍተቶች በመሙላት በሥራቸው ትርፋማ መሆን እንደቻሉ ገልጸዋል፡፡   በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ተቋማት አመራሮች ተገኝተዋል፡፡  
የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ የሚወስዱበት ነው
Aug 14, 2026 152
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ የሚወስዱበት መሆኑን በኢትዮጵያ እና በአፍሪካ ሕብረት የሳህራዊ ሪፐብሊክ አምባሳደር ላሚን ባአሊ ገለጹ። አምባሳደር ባአሊ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ እና በሌሎች ዘርፎች ስኬታማ ጉዞ እያደረገች እንደምትገኝ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ስኬታማ ጠቅላላ ምርጫ ማካሄዷንም አንስተዋል። ይህ ከፍተኛ የሕዝብ ተሳትፎ ዜጎች የፖለቲካ ኃላፊነታቸውን ለመወጣት ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ አዎንታዊ ማረጋገጫ እንደሆነም ነው የተናገሩት። በምርጫው የፖለቲካ ፓርቲዎች በንቃት መሳተፋቸውን በመጥቀስ፣ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ግንባታ ሂደት ውስጥ በጎ እርምጃ መሆኑንም አምባሳደር ባአሊ አስረድተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሚመራው የሪፎርም አጀንዳ በሀገሪቱ ውስጥ ለበለጠ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ ልማት ዕድገት አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። ከኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ጋር በተጣጣመ መልኩ የሚከናወኑ የተለያዩ የልማትና የለውጥ ሥራዎች አዎንታዊ ውጤት እያመጡ እንደሚገኙም ጠቁመዋል። በሀገሪቱ እየተተገበረ ያለው የኢኮኖሚ ሪፎርም የዜጎችን ኑሮ ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑን ጨምረው አንስተዋል፡፡ ይህ በኢትዮጵያ እውን እየሆነ ያለው ውጤታማ ሪፎርም በዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ዘንድ ከፍተኛ ትኩረትና እውቅና ማግኘቱን ተናግረዋል። በመሆኑም ይህ የኢትዮጵያ ስኬታማ ተሞክሮ በአጠቃላይ በአፍሪካ ደረጃ የሚገኙ ሌሎች ሀገራት ትምህርት ሊወስዱበት የሚችል ነው ብለዋል። ሀገራዊ ምክክር አስፈላጊ የፖለቲካ ልምምድ እንደሆነ የጠቆሙት አምባሳደሩ፣ በኢትዮጵያ እየተደረገ የሚገኘው ሀገራዊ ምክክር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። የሀገራዊ ምክክር ሂደቱ ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠርና ለሁሉም አካላት ዘላቂ ጥቅም ለማስገኘት ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ እንደሆነ ተናግረዋል። በሳህራዊ ሪፐብሊክ እና በኢትዮጵያ መካከል እ.ኤ.አ ከ1970ዎቹ ጀምሮ የነበረውን ትብብር አውስተው፣ የሀገራቱ ግንኙነት ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቅሰዋል። ባህል፣ ስፖርት፣ ንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ጤና እና ሌሎች የጋራ ፍላጎት በሆኑ ዘርፎች የሁለትዮሽ ትብብሩን የበለጠ ለማስፋት እንደሚሰራም አምባሳደር ላሚን ባአሊ ገልጸዋል።
በድሬደዋ የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ነው
Aug 14, 2026 153
ድሬደዋ፣ ነሐሴ 8/2018(ኢዜአ)፡- በድሬደዋ የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ መሆናቸውን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የድሬዳዋ አስተዳደር የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ ተናገሩ። በድሬዳዋ "ከሥራ ጠባቂነት ወደ ሥራ ፈጣሪነት" በሚል መሪ ሐሳብ የወጣቶችን ሥነ-ልቦናዊ የሥራ ላይ ብቃት የሚያጠናክር ሥልጠና እየተሰጠ ነው።   በወቅቱም በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የድሬዳዋ አስተዳደር የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ እንደተናገሩት፤ የወጣቶች ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ነው። በአስተዳደሩ ገጠርና ከተማ የሚገኙ ወጣቶችን በግብርና፣ በኢንዱስትሪና በአገልግሎት ዘርፎች ተሰማርተው ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተሠሩ የሚገኙ ሥራዎች ውጤታማ መሆናቸውን አንስተዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ በመተግበር ላይ የሚገኘው "ብቃት የሥራ ላይ የወጣቶች ሥልጠና" ለወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራ አበርክቶው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል።   ለአራተኛው ዙር የተመለመሉ ወጣቶች የተፈጠረላቸውን የሥራ ዕድል በመጠቀም ራሳቸውንና ሀገራቸውን ለመለወጥ በቁርጠኝነት የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሮቤል ጌታቸው በበኩላቸው፤ ባለፉት ሦስት ዙሮች የሥራ ላይ የሥልጠና መርሃ-ግብር ከ2 ሺህ 900 በላይ ወጣቶችን የሥራ ባለቤት ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። በዚህም ከተለያዩ ኢንዱስትሪዎች እና ተቋማት ጋር በማስተሳሰር የሥራ ላይ ክህሎትና ዕውቀት እንዲቀስሙ የተሰራው ስራ ውጤታማ ነበር ብለዋል።   የዛሬ ተመልማዮችም ከተቋምና እና ኢንዱስትሪዎች ጋር በመተሳሰር የ6 ወራት የሥራ ላይ ብቃታቸውን በማረጋገጥ የሥራ ባለቤት እንደሚሆኑም ጠቁመዋል። ዘንድሮም ለአራተኛ ዙር ሥልጠና የተመለመሉ 1 ሺህ 800 ወጣቶች በአስተዳደሩ ሁለት የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች መሠረታዊ ክህሎት መር ሥልጠና ተሰጥቷቸው ለሥራ ላይ ልምምድ ዝግጁ መደረጋቸውን ገልጸዋል። በቢሮው የሥራ ዕድል ፈጠራና የአንድ ማዕከል አገልግሎት ዳይሬክተር አቶ ሰኢድ አሊ፤ የድሬዳዋ አስተዳደር ለወጣቶች የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ያሳየውን ቁርጠኝነት የፌደራል መንግሥት በማረጋገጡ በየዓመቱ ተጠቃሚ ሲደረጉ የነበሩ ወጣቶችን ቁጥር ከ970 ወደ 1 ሺህ 800 ከፍ እንዲል ማድረጉን አስረድተዋል። የፕሮጀክቱ ተጠቃሚ ከሆኑት ወጣቶች መካከል ወጣት በአምላክ አምሳሉ እና ወጣት አፈንዲ ሙሳ፤ የተፈጠረላቸውን ምቹ አጋጣሚ በመጠቀም ራሳቸውንና ሀገራቸውን ለማሳደግ በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።    
የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ኢትዮጵያን ከገናና የዕድገት እና ሥልጣኔ ታሪኳ ጋር የማስታረቅ የሕልውና ጉዳይ ነው
Aug 14, 2026 228
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ኢትዮጵያን ከገናና የዕድገትና ሥልጣኔ ታሪኳ ጋር የማስታረቅ የሕልውና ጉዳይ መሆኑን በውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት የአፍሪካ ቀንድ እና የውኃ ጂኦፖለቲካ ከፍተኛ ተመራማሪ ጋሻው አይፈራም (ዶ/ር) ገለጹ። ጋሻው አይፈራም (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ ከሦስት አስርት ዓመታት በፊት ከገናና ሥልጣኔዋ ጋር በእጅጉ የተቆራኘ የባሕር በር ባለቤት እንደነበረች አስታውሰዋል። በአክሱም ሥልጣኔ ወቅትም ሆነ ከዚያ በፊትና በኋላ በነበሩት ዘመናት፣ ኢትዮጵያ የንግድና የውጭ ግንኙነቷን በቀይ ባሕር ቀጣና በባሕር በርና የወደብ አገልግሎቶች አማካኝነት ታሳልጥ እንደነበር ገልጸዋል። የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ለማሳጣት የውስጥ እና የውጭ ባዕዳን ኃይሎች በየዘመናቱ ያልሸረቡት ሴራና ያልፈነቀሉት ድንጋይ እንዳልነበርም አስረድተዋል። ታሪካዊ ጠላቶች የሚሸርቡትን ሴራ በመመከትና በማክሸፍ፣ ኢትዮጵያ አስተማማኝ የባሕር በር ባለቤትነቷን ለሺህ ዘመናት አስጠብቃ መቆየቷን አብራርተዋል። ሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድንና የሻዕቢያ ስብስብ ያለምንም ተጨባጭ ማስረጃም ሆነ አመክንዮ ኢትዮጵያ የባህር በር እንድታጣ ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል። በዚህም ኢትዮጵያን ከገናና ታሪክና ሥልጣኔዋ ጋር በእጁጉ ከተቆራኘው ቀይ ባሕር እንድትገለል መድረጉን አመልክተው፤ በሀገሪቷ ብሔራዊ ጥቅምና ፍላጎት ላይ ታሪክ ይቅር የማይለው በደል መፈጸሙን አስታውሰዋል። በኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ላይ የተፈጸመው ክህደትም በሀገሪቷ ዕድገትና ብልፅግና፣ በንግድና ኢንቨስትመንት፣ በገቢና ወጪ ንግድ እንቅስቃሴ ላይ እንቅፋት መፍጠሩን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ባሕር በር አልባነት ከሀገሪቷ የንግድና የሎጂስቲክስ አቅም ጋር ተያይዞ በገቢና ወጪ ንግድ ላይ ከፍተኛ የወደብ ኪራይና ሌሎች የገንዘብ ወጪዎችን እንድታወጣም እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በሌላ መልኩም በምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና የሚንቀሳቀሱ የሽብር ኃይሎች የሚፈጥሩትን የሰላምና ደኅንነት ስጋት ለመመከት ከባሕር በር ባለቤትነት መገለሏ የሚያሳድረው ተጽዕኖ ቀላል የሚባል እንዳልሆነ ገልጸዋል። በዚህም የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ የቅንጦት ሳይሆን የትውልድን መጻኢ ዕጣ ፈንታ የሚወስን የብሔራዊ ጥቅምና የህልውና ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል። የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄው የታሪክ ስብራትን የማረምና ኢትዮጵያን ከገናና ታሪክና ሥልጣኔዋ ጋር የማስታረቅ ጉዳይም ጭምር መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስርን በማጠናከር የአፍሪካን ኢኮኖሚ ውህደት ለማሳለጥ በምታደርገው ጥረት የባሕር በር ባለቤትነትን ጥያቄውን ምላሽ ማስገኘት እንደሚያስፈልግ አስረጂ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም ቀጣናዊ ሰላምና ደኅንነት፣ የጋራ ዕድገትና ብልፅግናን ማረጋገጥ የዚህ ትውልድ ሀገራዊ ኃላፊነት መሆኑንም አስገንዝበዋል። የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄው ዓለም አቀፍ ቅቡልነት እያገኘ ነው ያሉት ምሁሩ፤ ለዚህም ሀገራት፣ ዓለም አቀፍ ተቋማትና መገናኛ ብዙኅን የጉዳዩን አስፈላጊነት በቅጡ መገንዘባቸውን አብራርተዋል። በቀጣይም በጋራ ተጠቃሚነት መርህ የሚደረጉ የዲፕሎማሲ ጥረቶች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ መክረዋል። ለዚህም ኢትዮጵያውያን በሁሉም መስክ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄውን በበለጠ በማስገንዘብ የሀገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ በትብብር መሥራት እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል።
በአማራ ክልል ከ337 ሺህ ሄክታር በላይ የኮትቻ አፈርን በማንጣፈፍ ሰብል ማልማት ተችሏል
Aug 14, 2026 191
ባህርዳር ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ከ337 ሺህ ሄክታር በላይ የኮትቻ አፈርን በማንጣፈፍ ሰብል ለማልማት መቻሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በኢትዮጵያ ደጋማ አካባቢዎች በስፋት የሚገኘውና ከፍተኛ ለምነት ያለው የኮትቻ አፈር፣ ተገቢው የአፈርና ውሃ እንክብካቤ ከተደረገለት የሀገሪቱን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት የማፋጠን አቅም እንዳለው የዘርፉ ምሁራን ይገለፃሉ፡፡ አርሶ አደሮች ዘመናዊ የውሃ ፍሳሽና የቴክኖሎጂ ዘዴዎችን በመጠቀም ምርታማነታቸውን እንዲያሳድጉ አዳዲስ አሰራሮች በመተግበር ላይ መሆናቸው ይታወቃል። የቢሮው የአፈር ለምነት ባለሙያ አቶ አምሳሉ አድማስ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በኮትቻ አፈር የተሸፈነን መሬት በዘመናዊና በባህላዊ መንገድ በማንጣፈፍ በሰብል የማልማት ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል።   በዘንድሮው የመኸር እርሻ 689 ሺህ 533 ሄክታር የኮትቻ አፈርን በማንጣፈፍ ለማልማት ታቅዶ በተከናወኑ ተግባራት እስካሁን ከ337 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰብል ማልማት መቻሉን ተናግረዋል። በዚሁ የኮትቻ አፈር ልማት ላይ ከ468 ሺህ የሚበልጡ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ ሲሆን፤ ስንዴ፣ ገብስ፣ ጤፍ፣ ቦሎቄ፣ ባቄላ እና ሌሎችንም ሰብሎች እያለሙ ይገኛሉ። እስከያዝነው ወር ማብቂያ ድረስም በዕቅድ የተያዘውን መሬት አጠንፍፎ በጤፍና በሌሎች ዘግይተው በሚዘሩ ሰብሎች በማልማት የተሻለ ምርት ለመሰብሰብ ጥረት እየተደረገ እንደሆነ አክለው ገልጸዋል። የባሕር ዳር ዙሪያ ወረዳ አርሶ አደር ጌታሁን መንግሥት በበኩላቸው፤ ግማሽ ሄክታር የሚሆነውን የኮትቻ ጥቁር አፈር መሬታቸውን በማንጣፈፍ የስንዴ ሰብል እያለሙ መሆናቸውን ተናግረዋል።   ለዓመታት ውሃ ተኝቶበት ይከርም የነበረውን መሬት ዘመናዊ የእርሻ መሣሪያን ተጠቅመው በማንጣፈፍ ማልማት ከጀመሩ ወዲህ እስከ 18 ኩንታል ምርት ማግኘት መቻላቸውንም ገልጸዋል። በተመሳሳይም በማዕከላዊ ጎንደር ዞን የምሥራቅ ደንቢያ ወረዳ አርሶ አደር ልንገር ወርቁ፤ ቀደም ሲል ውሃ ይተኛበት የነበረውን የኮትቻ አፈር መሬታቸውን በማንጣፈፍ ስንዴ፣ ጤፍና ቦሎቄ በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። በዘንድሮው የመኸር እርሻም መሬታቸውን በማንጣፈፍ በስንዴና በጤፍ ያለሙ ሲሆን፣ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል። የቢሮው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ በክልሉ በ2017/2018 የምርት ዘመን በዘመናዊ የእርሻ መሣሪያና በባህላዊ ዘዴ ውሃን በማንጣፈፍ ከለማው 600 ሺህ ሄክታር ገደማ መሬት አበረታች ምርት ተገኝቷል።
የመዲናዋ አስደናቂ ልማት መንግስት የዜጎችን የኑሮ ዘይቤ ለማሻሻል ያለውን ቁርጠኛ አቋም የሚያሳይ ነው
Aug 14, 2026 197
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ የሚከናወኑ አስደናቂ የልማት ስራዎች መንግስት የዜጎችን የኑሮ ዘይቤ ለማሻሻል ያለውን ቁርጠኛ አቋም የሚያሳይ መሆኑን ጎብኚዎች እና ነዋሪዎች ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የእንጦጦ-ቀበና የወንዝ እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት መርቀው በይፋ ለህዝብ ክፍት ባደረጉበት ወቅት፣ ፕሮጀክቱ የግንባታ ስኬት ብቻ ሳይሆን መዲናችንን የአየር ንብረት ለውጥ የምትቋቋም ያደርጋል ብለዋል።   በተጨማሪም አዲስ አበባን ለነዋሪዎቿ ምቹና ዓለም አቀፍ የቱሪዝም እና የኢኮኖሚ ማዕከል ለማድረግ የሚደረገውን ስልታዊ ሽግግር እንደሚያፋጥንም ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የቀበና ወንዝ የቀድሞ ገጽታ በመቀየሩ ምክንያት ልዩ ልዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በቀን እና በምሽትም የሚዝናኑበት፣ የሚያሰላስሉበት እና ማህበራዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮችን የሚከውኑበት ማራኪ ስፍራ ሆኗል።   ኢዜአ ያነጋገራቸው ጎብኚዎችና የከተማዋ ነዋሪዎች፣ ይህ አስደናቂ የልማት ስራ መንግስት የዜጎችን የኑሮ ዘይቤ ለመቀየር የሚያደርገውን ቁርጠኛ አቋም የሚያሳይ ነው ብለዋል። የቱሪስት አስጎብኚዋ ምሕረት አሰፋ እንዳሉት፣ በአዲስ አበባ በጥቂት ዓመታት ውስጥ የተከናወኑት የልማት ስራዎች እጅግ አስደናቂ ናቸው። በሌሎች አገራት በጉብኝት ወቅት የተመለከተቻቸውን የከተማ ልማት ስራዎች በኢትዮጵያም ማየቷ እንዳስደሰታት ተናግረዋል። እነዚህ የመዝናኛ ስፍራዎች ከቱሪዝም ባሻገር ለህብረተሰቡ ንጹህ አካባቢ በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አንስተዋል። ህጻናት እና ታዳጊዎች በአስተማማኝ ሁኔታ የሚጫወቱባቸውና ነዋሪዎችም ለጤናቸውና ለዕረፍት የሚጠቀሙባቸው ስፍራዎች መፈጠራቸው መንግስት ለዜጎች የሰጠውን ልዩ ትኩረት የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል። የቀድሞው የቀበና ወንዝ አካባቢ በቆሻሻ የተሞላ እንደነበር የሚያስታውሰው ሌላኛው የአዲስ አበባ ነዋሪ መለሰ ከበደ፣ አሁን ላይ ግን አካባቢው ውብ እና ለኑሮ ተስማሚ መሆን መቻሉን ተናግረዋል።   ይህ የልማት ስራ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች ያሉት በመሆኑ፣ ለቱሪዝም እና ለወጣቶች የስራ ዕድል ፈጠራ ምቹ ሁኔታን የፈጠረ መሆኑም አንስተዋል። በአካባቢው እንደመኖራቸው መጠን ከቤተሰባቸው ጋር በመሆን በቀበና ወንዝ አካባቢ የሚያሳልፉት ጊዜ እጅግ አዝናኝ እና አስደሳች መሆኑንም ገልጸዋል። እንዲህ ያሉ አዳዲስ የመዝናኛ ስፍራዎች ጤናማ ትውልድ እና አካባቢን ለመፍጠር ወሳኝ ሚና ይጫወታሉ ብለዋል። እሸቱ አማረ በበኩላቸው፣ ቀደም ባሉት ጊዜያት በአዲስ አበባ እንዲህ ያሉ ዘመናዊ የመዝናኛ ሥፍራዎች እጥረት በመኖሩ ነዋሪዎች ከከተማ ውጭ ወደ ሆኑ አካባቢዎች ለመሄድ ይገደዱ እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ግን በአዲስ አበባ እንዲህ ያለ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩ ለከተማዋ ነዋሪዎች እፎይታን የሰጠ ነው ብለዋል።   በተለይም ህጻናት አእምሯቸውን የሚያድሱበትና ንጹህ አየር የሚያገኙበት በመሆኑ ለዕድገታቸውም ሆነ ለጤናቸው ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተዋል። ከአራት ዓመት በኋላ ዳግም አዲስ አበባን የጎበኙት ከድሬዳዋ የመጡት ሁስኒያ አብዲ፣ የከተማዋ ገጽታ በኮሪደር ልማት ስራዎች ተቀይሮ መመልከታቸው እንዳስደነቃቸው ተናግረዋል። በዋና ዋና መንገዶች ላይ የተከናወኑት የኮሪደር ልማት እና የጽዳት አጠባበቅ ከተማዋን እጅግ ውብ እና ሳቢ እንዳደረጓትም ገልጸዋል። ከባሌ ሮቤ የመጡት ሁሴን አህመድ፣ ከጥቂት ዓመታት በፊት በነበረው እና አሁን ባለው የከተማዋ ዕድገት መካከል ያለውን ልዩነት በግልጽ መመልከታቸውን ገልጸዋል። በስራ ምክንያት አድካሚ ቀናትን የሚያሳልፉ የተለያዩ ሰራተኞች፣ ከስራ ውጪ አእምሯቸውን ዘና የሚያደርጉበትና የሚያሳርፉበት ቦታ ማግኘታቸው እጅግ አስደሳች መሆኑን ተናግረዋል። ይህ ለመዲናችን ውበትን ከማጎናጸፍ ባለፈ የቱሪዝም መዳረሻ በመሆን ለሀገራችን ዕድገት ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ታዳሽ ኃይል የማመንጨት አቅሟን በማሳደግ የቀጣናው የኃይል ማዕከል እየሆነች ነው
Aug 14, 2026 247
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ማመንጨት አቅሟን በማሳደግ የቀጣናው የኃይል ማዕከል እየሆነች መምጣቷን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጅነር ሃብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ የውሃ፣ የፀሐይ፣ የነፋስና የጂኦተርማል ብዝኅ የኃይል ፀጋዎች ልማት የኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅምን ማጎልበት የሚቻልበት ምኅዳር እየፈጠረ ይገኛል። የታዳሽ ኃይል ልማት እመርታዊ ጉዞም የኤሌክትሪክ ማመንጨትን ከልማት፣ ልማትን ከኢኮኖሚ ዕድገት፣ ኢኮኖሚ ዕድገትን ከቀጣናዊ ትስስር ጋር እያሰናሰለ የሚገኝ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ግብ ነው። ሚኒስትር ኢንጅነር ሃብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፣ የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ልማት ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር ዘላቂ ኢኮኖሚ እንድትገነባ እያስቻለ ነው።   የታዳሽ ኃይል ምንጮቹን በማቀናጀት የሚካሄደው ልማትም የኢንዱስትሪ፣ የግብርና፣ የከተማ ልማትና የዲጂታል ኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥን የኃይል መሠረተ ልማት እየገነባ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የውሃ፣ የፀሐይ፣ የነፋስና የጂኦተርማል ሃብቶችን በማልማት የኤሌትክትሪክ የኃይል ምንጮችን፣ ደህንነትና ዘላቂነትን በማጎልበት የኢኮኖሚ መሠረት መፍጠር እየተቻለ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም በዜጎች ትብብርና በሀገር አቅም የተገነባው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በኢትዮጵያ የኃይል ልማት ታሪክ አዲስ ምዕራፍ መክፈቱን አስረድተዋል። የሕዳሴ ግድብ የኃይል አቅርቦት አቅም የኢትዮጵያን ፍላጎት ለማሟላት ከማገዙ ባሻገር፣ ኃይልን ወደ ጎረቤት ሀገራት በመላክ የቀጣናዊ ኢኮኖሚ ትስስርን ለማጠናከር አዲስ ዕድል መፍጠሩን አስረድተዋል። ይህም ኃይል ለኢትዮጵያ ዕድገትና ልማት የሚውል ግብዓት ብቻ ሳይሆን የንግድ፣ የዲፕሎማሲና የቀጣናዊ ትብብር መሣሪያ እየሆነ መምጣቱን እንደሚያመላክት አብራርተዋል።   የዓለም አቀፍ የውሃና የኃይል ገበያ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታን ታሳቢ በማድረግም ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ፀጋዎቿን በማልማት ከሀገር ውስጥ የኃይል ፍላጎት ባሻገር ቀጣናዊ ትስስርን እያሰፋች መሆኗን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ልማት እመርታዊ ጉዞም ኃይልን ከማመንጨት የተሻገረ ቀጣናዊ የጋራ ዕድገትና ብልፅግናን የማፋጠን አህጉራዊ የልማት ግብ መሆኑንም አስገንዝበዋል። በዚህም ስትራቴጂካዊ የተፈጥሮ ፀጋዎችን በማልማት የራሷን የኃይል ደህንነት ከማረጋገጥ ባሻገር ለምስራቅ አፍሪካ የኃይል ትስስርና ለአፍሪካ ኢኮኖሚ ውህደት የሚያግዝ አዲስ ምዕራፍ እየገነባች ነው ብለዋል። ለአብነትም ከጅቡቲ፣ ኬንያና ሌሎች ጎረቤቶች ጋር ያለውን የኃይል ትስስር በማስፋፋት የጋራ ዕድገትና ብልፅግናን የሚያጎለብቱ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በቀጣይም ደቡብ ሱዳንና ሶማሊያን ጨምሮ ለጎረቤት ሀገራት የኤሌክትሪክ ኃይል ለማቅረብና የኃይል ትስስር መሠረተ ልማትን ለማስፋፋት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። የኃይል ሽያጩም ኢትዮጵያን የኃይል ማዕከል በማድረግ የውጭ ምንዛሬ ገቢ ምንጭ በመሆን ጭምር ከኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ጋር ተሰናስሎ መቀጠሉን ተናግረዋል።
በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው የበልግ ወቅት ከለማው መሬት እስካሁን ከ21 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቧል
Aug 14, 2026 277
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው የበልግ እርሻ በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥ እስካሁን ከ21 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በኦሮሚያ ክልል የበልግ እርሻ ልማት ለአርሶና አርብቶ አደሩ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ምንጭና የምግብ ዋስትና መሰረት ነው። በክልሉ በበልግ ዝናብ የሚከናወነው ይህ የግብርና እንቅስቃሴ አርሶ አደሩ የምግብ ፍላጎቱን እንዲሸፍን ከማስቻሉም በላይ፣ ገበያን ለማረጋጋት የሚኖረው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው። በተለይም እንደ ቦረና፣ ጉጂና አርሲ ባሉ አካባቢዎች በበልግ እርሻው የከብት መኖን ከማልማት ባሻገር ዋና ዋና የህብረተሰቡ የፍጆታ ሰብሎች የሚመረቱበት በመሆኑ ለክልሉ ግብርና መነቃቃት ቁልፍ ሚና ይጫወታል።   ክልሉ የዘመናዊ ቴክኖሎጂ እና የሜካናይዜሽን አጠቃቀምን በማስፋት፣ የአርሶ አደሩን የሙያ ብቃት በማሳደግ እና የግብርና ግብዓቶችን በወቅቱ በማቅረብ ረገድ ያሳየው ቁርጠኝነት ለአፈፃፀሙ መሳካት ዋና ምክንያት ሆኗል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ በበልግ ወቅት ወደ ሁለት ሚሊዮን ሄክታር የሚጠጋ መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ለምቶ ወደ ምርት መሰብሰብ ተገብቷል። ለበልግ እርሻው ውጤታማነት ለአርሶ አደሩ የሙያ ብቃትን የሚያሳድጉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናዎች የተሰጡ ሲሆን፣ ባለሙያዎች በመስክ በመገኘት ያልተቋረጠ ሙያዊ ድጋፍና ክትትል ሲያደርጉ መቆየታቸውን ተናግረዋል። ምርትና ምርታማነትን የሚጨምሩ የግብርና ግብዓቶች በወቅቱ ለአርሶ አደሩ እንዲደርሱ መደረጉን ጠቁመው፤ ከዚህ በተጨማሪም ሰብሉን ከተባይና ከአረም ለመጠበቅ የሚያስችሉ የፀረ-ተባይና የፀረ-አረም መድሃኒቶች አቅርቦት መመቻቸቱን ገልጸዋል።   በዚህም በዘንድሮው የበልግ እርሻ በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥ ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ በሚሆነው ላይ የደረሱ ሰብሎች የተሰበሰቡ ሲሆን፣ ከዚህም 21 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ማግኘት መቻሉን ገልጸዋል። የምርት አሰባሰቡን ቀልጣፋና ከብክነት የጸዳ ለማድረግ በግብርና ሜካናይዜሽን አማካኝነትና የሰው ኃይልን በማቀናጀት እየተካሄደ እንደሚገኝ አንስተዋል። እስካሁን ከተሰበሰቡት ዋና ዋና ሰብሎች መካከል፡ ጤፍ፣ስንዴ፣ገብስ፣ሰሊጥ፣ማሾ እና ሌሎችም ይገኙበታል ብለዋል። በኦሮሚያ ክልል የበልግ እርሻው በስፋት የተካሄደው በ11 ዞኖች ውስጥ ሲሆን፤ ከእነዚህም መካከል የቦረና፣ ጉጂ፣ ምዕራብ አርሲ፣ ባሌ እና የምስራቅ ሐረርጌ ዞኖች በዋናነት ተጠቃሽ መሆናቸውን አክለዋል። በቀጣይም ቀሪዎቹን የሰብል ምርቶች በወቅቱና ያለ ብክነት ለመሰብሰብ የተጀመረው የተቀናጀ ድጋፍና ክትትል ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ቢሮው አስታውቋል።
በካፋ ዞን የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የአርሶ አደሮችን ገቢ እያሳደገ ነው
Aug 14, 2026 181
ቦንጋ ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦በካፋ ዞን ገዋታ ወረዳ በሌማት ትሩፋት መርሀግብር የተሰማሩ አርሶ አደሮች ምርትና ምርታማነታቸው እያደገ በመምጣቱ ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆኑን ተናገሩ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ግብርና ቢሮ በበኩሉ በክልሉ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርን ውጤታማ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት ምርትና ምርታማነት እያደገ መምጣቱን አስታውቋል። በካፋ ዞን ገዋታ ወረዳ መሻማሊ ቀበሌ በዓሣ ልማት ላይ የተሰማሩት አርሶ አደር አባቢያ አባጨብሳ እንዳሉት፤ በሌማት ትሩፋት መርሀግብር በጓሯቸው ለአሣ እርባታ የሚሆን ኩሬ በማዘጋጀት አሣ እያመረቱ ነው፡፡   ምርቱን ለቤት ውስጥ ፍጆታ ከማዋል ባለፈ ለሽያጭ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። መንግስታዊ ካለሆነ ድርጅት በተደረገላቸው ድጋፍ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር ተጨማሪ ኩሬዎችን በማዘጋጀት የዓሣ ልማት ሥራቸውን ማስፋፋታቸውን ገልጸዋል። በወረዳው ሒንጊዶ ቀበሌ በዶሮ እርባታ ሥራ የተሰማሩት አርሶ አደር ብርሃኑ ወልደሰንበት በበኩላቸው፣ ከዚህ ቀደም በባህላዊ መንገድ ዶሮዎችን ሲያረቡ ለአውሬ ይጋለጡ እና የእንቁላል ምርታቸውም ዝቅተኛ እንደነበር ተናግረዋል።   አሁን ግን ባገኙት ሙያዊ ድጋፍ ታግዘው የዶሮ ቤት በማዘጋጀትና የተመጣጠነ መኖ ተጠቅመው በማርባታቸው የእንቁላል ምርትና ምርታማነትን ማሳደጋቸውን ገልጸዋል። ያመረቱትን እንቁላል ለቤት ውስጥ ፍጆታ ከማዋል ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል። በንብ ማንብ ሥራ ላይ የተሰማሩት የዶማ ቀበሌ አርሶ አደር ዳንኤል ቶሌ በበኩላቸው፣ በአምስት ባህላዊ ቀፎዎች ሥራ እንደጀመሩ ገልፀው የሌማት ትሩፋት መርሀግብር ሥራቸውን ለማስፋፋት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል።   በመርሀግብሩ በተደረገላቸው የንብ ቀፎና ሙያዊ ድጋፍ ታግዘው በአሁኑ ወቅት ከ50 በላይ ዘመናዊና ባህላዊ ቀፎዎች እንዳሏቸው ገልፀዋል። ከዚህም በዓመት ሁለቴ ማር እንደሚሰበስቡ ገልጸው፣ በአንድ ዙር ብቻ ከሚሰበስቡት የማር ምርት እስከ 168 ሺህ ብር ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል። የሌማት ትሩፋት መርሀግብር ከተጀመረ ወዲህ በክልሉ 2ሺህ 763 የወተት፣ የዶሮ፣ የዓሣ፣ የማር እና የከብት ሥጋ መንደሮችን በማደራጀት ከ130 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለ የገለጹት ደግሞ በክልሉ ግብርና ቢሮ የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ ሀላፊ አቶ ታመነ በቀለ ናቸው።   መንደሮችን ከማደራጀት ባለፈ ለአርሶ አደሩ ስልጠና በመስጠት፣ በግብዓት አቅርቦት እንዲሁም የተጠናከር የድጋፍና ክትትል ሥራ በመሰራቱ በሁሉም ፓኬጆች ጥሩ መሻሻሎች ታይተዋል ብለዋል፡፡ በተለይም የዝርያ ማሻሻያ ፣ የአረንጓዴና ምጥን መኖ ልማትና አቅርቦት ላይ ልዩ ትኩረት በመሰጠቱ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት በከፍተኛ መጠን ማሳደጉን አቶ ታመነ ተናግረዋል። በዚህም የሌማት ትሩፋት ኢንሼቲቭ ከመጀመሩ በፊት በክልሉ በዓመት ይመረት የነበረው የወተት ምርት ከ307 ወደ 392 ሚሊዮን ሊትር ከፍ ማለቱን ጠቁመዋል። የእንቁላል ምርትን ከ335 ወደ 362 ሚሊዮን፣ የማር ምርት ከነበረበት 66 ሺህ ቶን ወደ 79 ሺህ ቶን እንዲሁም የዓሣ ሥጋ ምርትን ከ4ሺህ 615 ቶን በአማካይ ወደ 7ሺህ ቶን ለማሳደግ ተችሏል ብለዋል። ምርታማነት ማደጉም የህብረተሰቡ የምግብና ስነምግብ ሥርዓት እንዲሻሻል ከማድረግ ባለፈ ተኪ ምርትና የኤክስፖርት ምርቶች በመጠንና በጥራት እንዲያድጉ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል ብለዋል። በቀጣይም በተቀናጀ መልኩ የተጀመሩ ሥራዎችን አጠናክሮ በማስቀጠል የተሻለ ምርት በብዛትና በጥራት በማምረት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል።
የግብርና ቴክኖሎጂዎችንና የኩታ ገጠም አሠራርን በመጠቀማችን ምርታማነታችን ጨምሯል-አርሶ አደሮች
Aug 14, 2026 166
ጋምቤላ ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችንና የኩታ ገጠም አሠራርን በመጠቀማችን ምርታማነታችን ጨምሯል ሲሉ በጋምቤላ ክልል የአኙዋ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። አርሶ አደሮቹ፤ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችንና የኩታ ገጠም አሠራርን በመጠቀማቸው ምርታማነታቸው ጨምሮ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው ማደጉን ለኢዜአ ገልጸዋል። በዞኑ የአቦቦ ወረዳ ሞዴል አርሶ አደር ወይዘሮ አጁሉ ኪሩ በሰጡት አስተያየት፤ ቀደም ሲል በባህላዊ የአስተራረስ ዘዴ ሲያለሙ ከራስ ፍጆታ ያለፈ ምርት እንዳልነበራቸው ተናግረዋል።   ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመው ማልማት በመጀመራቸው የተሻለ ምርት እያገኙ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ዘንድሮም ካለሙት ማሳ ጥሩ ውጤት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። የእርሻ ትራክተር በመጠቀም በኩታ ገጠም እርሻ ሰሊጥ፣ በቆሎ፣ ሩዝ፣ ማሽላና ሌሎች ሰብሎችን በማልማት ከራሳቸው አልፈው ለገበያ እያቀረቡ እንደሚገኙ የጠቀሱት ደግሞ የዲማ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ወርቅነህ ይርዳው ናቸው። በዞኑ የአቦቦ ወረዳ የመንደር 13 አርሶ አደር አቶ በለጠ አባተ፤ የተሻሻሉ የግብርና አሠራሮችን በመከተል ሥራ ከጀመሩ ወዲህ ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በተለይም በክላስተር ተደራጅተው በጋራ ማምረት በመቻላቸው ተጠቃሚነታቸው እየጨመረ መምጣቱን አስረድተዋል። የአኝዋህ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ኝኬው ጊሎ፤ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሻሻል ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ይገኛል ብለዋል።   አርሶ አደሮቹ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅመው እንዲያመርቱ ዘመናዊ የእርሻ መሣሪያ አቅርቦት መመቻቸቱን ተናግረዋል። በዘንድሮው የምርት ዘመን መጠነኛ የዝናብ መቆራረጥ መከሰቱን የጠቀሱት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ፤ ይህንን ተከትሎ የምርት መቀነስ እንዳያጋጥም በአጭር ጊዜ በሚደርሱ ሰብሎች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑንም ገልጸዋል። በክልሉ የመኸር ወቅት ለማልማት ከታቀደው 180 ሺህ ሄክታር መሬት አብዛኛው በተለያዩ ሰብሎች መሸፈኑን ከክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በደቡብ ወሎ ዞን በመኸር እርሻ ከ224 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ ሰብል ለምቷል
Aug 14, 2026 179
ደሴ ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን በመኸር እርሻ ከ224 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ ሰብል መሸፈኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ይመር ሰይድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ዞኑ ለስንዴ ልማት ምቹና ተስማሚ የአየር ንብረት ባለቤት በመሆኑ የስንዴ ሰብል በስፋት እየለማ ይገኛል።   በዘንድሮው የመኸር ወቅት ከለማው አጠቃላይ መሬት ውስጥ 166 ሺህ 450 ሄክታሩ በኩታ ገጠም አሰራር የተሸፈነ ሲሆን፣ ከዚህም ከ9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይሰበሰባል ተብሎ ይጠበቃል። የኩታ ገጠም ልማት አርሶ አደሩ በወቅቱ ግብዓትና ሙያዊ ድጋፍ እንዲያገኝ፣ በጋራ ለማረስ እና ለመዝራት እንዲሁም ተባይና አረምን በትብብር ለመከላከል የሚረዳ ከመሆኑ ባሻገር ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑን ገልፀዋል። ይህም የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ትርፍ ምርት በማምረት ለገበያ ለማቅረብ የሚያስችል በመሆኑ አስፈላጊው ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩ ማሳውን በየቀኑ በማሰስና የአረም መከላከል ስራዎችን በማጠናከር ላይ እንደሚገኝ ነው ያመለከቱት።   በደሴ ዙሪያ ወረዳ የ015 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሰይድ እሸቱ ፤ አንድ ሄክታር ተኩል መሬታቸውን በኩታ ገጠም ዘዴ ስንዴ ማልማታቸውን ገልፀዋል። ከግብርና ባለሙያዎችም ድጋፍ እና ግብዓት በወቅቱ በማግኘታቸው ከ40 ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል። በተመሳሳይ በተንታ ወረዳ የ06 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መሀመድ አህመድ፤ አንድ ሄክታር መሬታቸውን በኩታ ገጠም አልምተዋል። ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን ማሳቸውን በዘር የሸፈኑ ሲሆን የተሻለ ምርት ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን ገልፀዋል። በደቡብ ወሎ ዞን በ2018/2019 የመኸር ወቅት በአጠቃላይ በተለያዩ ሰብሎች ከተሸፈነው 433 ሺህ ሄክታር መሬት ከ15 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን ከ184 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ሰብል በኩታ ገጠም ለምቷል
Aug 14, 2026 221
ነቀምቴ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦ በምስራቅ ወለጋ ዞን በ2018/19 የመኸር እርሻ ከ184 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ሰብል በኩታ ገጠም መልማቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። ምስራቅ ወለጋ ዞን ሰፊ እና ለም አመቺ የእርሻ መሬት እንዲሁም በቂ የዝናብ መጠን ካላቸውና ዋነኛ የግብርና ምርት ቀጠናዎች አንዱ ሲሆን፤ በአካባቢው በስፋት ከሚመረቱ ሰብሎች መካከል የበቆሎ ምርት በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። በዞኑ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ አርሶ አደሮችን በማደራጀት በኩታ ገጠም የእርሻ ዘዴ እንዲያለሙ፣ ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን፣ ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያን በስፋት እንዲጠቀሙ ለማስቻል ከፍተኛ እንቅስቃሴ ሲደረግ ቆይቷል። የምስራቅ ወለጋ ዞን ግብርና ፅህፈት ቤት ምክትል ሀላፊ ደረጄ ብርሃኑ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ በምርት ዘመኑ በዞኑ 831 ሺህ 816 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ተሸፍኗል።   በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥ 184 ሺህ 879 ሄክታሩ በኩታ ገጠም በበቆሎ ሰብል መሸፈኑን ጠቁመው፤ ከዚህም ወደ 10 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በምስራቅ ወለጋ ዞን በሚገኙ ሁሉም ወረዳዎች በስፋት ከሚመረቱ ሰብሎች መካከል የበቆሎ ምርት ዋነኛው መሆኑን ጠቁመው፣ እንደ ማሽላ፣ ጤፍ፣ ስንዴና ገብስ ያሉ የጥራጥሬ ሰብሎችና የቅባት እህሎችም በስፋት እንደሚመረቱ ገልጸዋል። አርሶ አደሩ ዘመናዊ የግብርና አሰራሮችን በመጠቀም ይበልጥ ውጤታማና ምርታማ እንዲሆን ለማስቻል፤ በየደረጃው በሚገኙ የግብርና ባለሙያዎች አማካኝነት የሚደረገው የሙያ ድጋፍ፣ የቴክኖሎጂና የግብዓት አቅርቦት እንዲሁም የቅርብ ክትትል ተጠናክሮ መቀጠሉን አክለው ገልጸዋል። በዞኑ የበቆሎ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ከቀረበው 550 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ 400 ሺህ ኩንታሉ ለአርሶ አደሮቹ መሰራጨቱን ተናግረዋል። ከምርጥ ዘር አንጻርም 32 ሺህ ኩንታል የበቆሎ ምርጥ ዘር መቅረቡን ገልጸው፣ በልማቱም ከ152 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን ጠቁመዋል።   በዞኑ በልማቱ እየተሳተፉ ከሚገኙት አርሶ አደሮች መካከል አርሶ አደር አብዱ ስጦታው እንደተናገሩት፤ ላለፉት ሁለት ዓመታት በኩታ ገጠም የአሰራር ዘዴ በቆሎን በስፋት ሲያለሙ ቆይተዋል። በዚህም ባለፈው ዓመት ምርታማነታቸው መሻሻሉንና ምርጥ ዘርን በመጠቀም ከአንድ ሄክታር መሬት እስከ 43 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን አንስተው፣ በዘንድሮው የምርት ዘመንም የተሻለ ውጤት ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አርሶ አደር አዲሱ ተሾመ በበኩላቸው፤ የግብርና ባለሙያዎችን ምክር ተግባራዊ በማድረግ የቀረበላቸውን ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያን በአግባቡ በመጠቀም ምርታማ ለመሆን በትጋት በመስራት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።
 በክልሉ ያለውን ሰፊ የቱሪዝም ሀብት ለማልማት እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ
Aug 14, 2026 177
ጋምቤላ፤ነሐሴ 8 /2018(ኢዜአ)፦በጋምቤላ ክልል ያለውን ሰፊ የቱሪዝም ሀብት በማልማት የታለመውን የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ስኬታማ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ቱሪዝም ቢሮ አስታወቀ። የመደመር መንግስት በቱሪዝም ዘርፍ፤ የትናንት የታሪክ ሀብትን፣ የዛሬውን ልማት እና የነገውን ብልጽግና በማቀናጀት ኢትዮጵያን ተወዳዳሪ የቱሪዝም መዳረሻ የማድረግ ግብ አለው። እሳቤው ቱሪዝምን ከቀደመው የተበታተነና የተወሰነ አካባቢ ላይ ብቻ ያተኮረ አሠራር በማውጣት፣ ከሌሎች አጠቃላይ የመሠረተ ልማት ዝርጋታዎች (እንደ መንገድ፣ አየር መንገድ እና ሆቴሎች) ጋር ተሳስሮ የሚተገበር ጉዳይ እንደሆነ ያሳያል። በእነዚህ አዳዲስ የቱሪዝም ፕሮጀክቶች አማካኝነት የሀገርን መልካም ገጽታ ከመገንባት ባለፈ፣ ለአካባቢው ማህበረሰብ ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠርና የውጭ ምንዛሬ ግኝትን በማሳደግ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን በማላቅ ውጤት እንዲያመጣ ተደርጎ ወደ ተግባር ተገብቷል። የጋምቤላን ጨምሮ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ለቱሪዝም ኢንዱስትሪው ልማት የሚውል ሰፊ የተፈጥሮና የሰው ሰራሽ የመስህብ ስፍራዎች ይገኛሉ። የጋምቤላ ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ ኮንግ ሬት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ያለውን ሰፊ የቱሪዝም ሀብት በማልማት የታለመውን የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ስኬታማ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ።   በተለይም በክልሉ እምቅ የብዝሃ ሕይወት ሀብት ያለውን የጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክን ከ"አፍሪካ ፓርክስ ኔትወርክ" ጋር በመቀናጀት ለማልማት ሰፊ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። አሁን ላይ በፓርኩ የሚገኙት የዱር እንስሳት የክረምትና የበጋ እንቅስቃሴያቸውን መሠረት ያደረገ የመዳረሻ ቦታዎችን ለማልማት በአውሮፕላን የታገዘ የቅኝት፣ የሰርቬይና የዳሰሳ ጥናት እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ በባዮስፌር የተመዘገቡትን የተፈጥሮ ደኖችን ጨምሮ ሌሎች የቱሪዝም መስህቦችን ለማልማት የጥናትና ልየታ ሥራዎች መከናወናቸውን የቢሮ ኃላፊው ገልጸዋል። በቢሮው የቱሪዝም መዳረሻ መሠረተ ልማት ቡድን መሪ አቶ ደርባቸው ሸዋለም በበኩላቸው፤ በክልሉ 109 የቱሪዝም መስህቦችን በጥናት በመለየት እንደየ ሀብት አቅማቸው በቅደም ተከተል ለማልማት ታቅዶ እየተሠራ ነው ብለዋል።   በተለይም ከፍተኛ የቱሪዝም አቅም ያለውን የጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ ያለበትን የመሠረተ ልማት ተግዳሮት ለመፍታትና የዘርፉን ሀብት በሚፈለገው ደረጃ ጥቅም ላይ ለማዋል ከ"አፍሪካ ፓርክስ ኔትወርክ" ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። በፓርኩ አቅራቢያ በሚገኘው በአሌሮ ግድብ ዘመናዊ የእንግዳ ማረፊያ ሎጆች ለመገንባት የግንባታ ግብዓቶች መቅረባቸውንም ገልጸዋል።
ከአረንጓዴ አሻራ እስከ ዓለም ገበያ - የኢትዮጵያ ቡና ልማት አዲስ የዕድገት ምዕራፍ
Aug 13, 2026 335
(በሙሴ መለሰ) ኢትዮጵያ የቡና መገኛ ከመሆኗም ባለፈ ምርቱ አሁንም ለሀገሪቱ ምጣኔ ሀብትና ማህበራዊ ህይወት ትልቅ መሰረት ያለው ነው። የዓለም የቡና ዝርያዎች ሁሉ መገኛ የሆነው የአረቢካ ቡና ለመጀመሪያ ጊዜ የተገኘውም በኢትዮጵያ እንደሆነ ይታወቃል። በኢትዮጵያ ቡና መጠጣት የዕለት ተዕለት ባህል ሲሆን፣ የቡና አፈላል ስነ ስርዓት ሰላምን፣ አንድነትንና ማህበራዊ ውይይትን የሚያጠናክር ትልቅ እሴት ተደርጎም ይወሰዳል። በአሁኑ ወቅት ቡና ለሀገሪቱ ከፍተኛውን የውጭ ምንዛሬ ገቢ የሚያስገኝ ቀዳሚው የግብርና ምርት በመሆን ማዕከላዊ የኢኮኖሚ ሚናውን እየተጫወተ ይገኛል። አብዛኛው የኢትዮጵያ ቡና የሚመረተው በተፈጥሯዊ መንገድ በገበሬዎች ማሳ ላይ ወይም በዱር ውስጥ በመሆኑ፣ ለሰው ሰራሽ ማዳበሪያና ኬሚካል ተጋላጭ አይደለም። ይህም በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለውን ተመራጭነት ይበልጥ ከፍ አድርጎታል። ከኢትዮጵያ የወጪ ንግድ ምሰሶ አንዱ የሆነው ቡናችን ለሀገሪቷ እያስገኘ ያለው ገቢም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከምክር ቤቱ ለተነሱላቸው ጥያቄዎች በሰጡት ማብራሪያ ካነሷቸው ጉዳዮች መካከልም አንዱ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዋልታ የሆነው ቡና ነበር። ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከብራዚልና ኮሎምቢያ በመቀጠል በዓለም 3ኛዋ ትልቋ የቡና ላኪ ሀገር መሆኗን እና በአፍሪካም ቀዳሚ ደረጃ ላይ መቀመጧን ገልጸዋል። በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ከቡና ወጪ ንግድ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ የተገኘ ሲሆን፣ ይህ ውጤት ባለፉት 17 ዓመታት በድምሩ ከተገኘው 3 ነጥብ3 ቢሊዮን ዶላር ጋር ሲነጻጸር በዘርፉ የተመዘገበውን ከፍተኛ ዕድገት ያሳያል ብለዋል። ለተመዘገበው ውጤት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱ የተጠቀሰ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ በዘርፉ ያላትን እምቅ አቅም አጠናክራ መጠቀም እንዳለባት ተናግረዋል። የግብርና ሚኒስትሩ አዲሱ አረጋ የኢትዮጵያን የቡና ዘርፍ ከዘልማዳዊ አሰራር ወደ ዘመናዊ ምርታማነት ለማሸጋገር የሚያስችል አዲስ የ10 ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ እና የተሻሻለ የልማት ፓኬጅ መዘጋጀቱን በቅርቡ ባስተላለፉት መልዕክት ገልጸዋል። ቡና በሀገሪቱ ኢኮኖሚ፣ የሚሊዮን አርሶ አደሮች የኑሮ መሠረትና የወጪ ንግድ ዋነኛ ምሰሶ መሆኑን ጠቅሰው ይህንን ታላቅ ሀብት በጥራትና በዘላቂነት በማሳደግ ከምርት ወደ እሴት፣ ከእሴት ወደ ዓለም ገበያ ማሸጋገር የዘርፉ ዋነኛ አቅጣጫ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንኑ ስትራቴጂ ለማሳካት የተጀመረው ሃገራዊ የቡና ምርትና ምርታማነት ኢኒሼቲቭ በአሁኑ ወቅት በሔክታር 9 ኩንታል የሆነውን የቡና ምርታማነት ወደ 21 ኩንታል ለማሳደግ ያለመ መሆኑን ሚኒስትሩ አብራርተዋል። በተጨማሪም በ 1 ነጥብ15 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ላይ የቡና ልማት ለማካሄድ የታቀደ ሲሆን፣ ለዚህም ምርጥ የቡና ዘር አጠቃቀም፣ የተቀናጀ የአፈር ንጥረ-ነገር፣ የቡና ተክል ጥግግት፣ የገረዛና የጥላ ዛፍ አያያዝ፣ የተቀናጀ የተባይ መከላከል፣ የመስኖ፣ የማዳበሪያ እንዲሁም የተሻሻለ የምርት አሰባሰብና የዕድሳት ሥራዎችን ያካተቱ ዘጠኝ የትኩረት መስኮች ተለይተው ወደ ሥራ መግባታቸውን አመልክተዋል። ይህ አዲሱ የቡና ልማት ኢኒሼቲቭ አርሶ አደሮችን፣ የማህበራትንና የባለሙያዎችን ግንዛቤና አቅም ለማሳደግ ሰፊ የንቅናቄ ሥራዎችን እንደሚከናውን ሚኒስትሩ ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በቡና ወጪ ንግድ ከአፍሪካ ቀዳሚና ከዓለም 3ኛዋ ትልቅ ላኪ ሀገር በመሆን ያሳየችው እመርታ፣ የዘርፉን ታላቅ የምጣኔ-ሀብት አቅም በተጨባጭ የሚያሳይ ነው። ለዚህ ደግሞ ላለፉት ዓመታት የተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የተፈጥሮን ምህዳር በማስተካከል ረገድ የራሱን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱ ይታወቃል። በዚህም መርሃ-ግብሩ በተጀመረበት 2011 ዓ.ም 600 ሺህ ሔክታር መሬት ላይ የተተከለው የቡና ችግኝ በየዓመቱ እያደገ በመሔድ በ2017 ዓ.ም ላይ 1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር መሸፈን ተችሏል። ይሄ በመሆኑም የቡና ምርታማነት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል። በ2011 ዓ.ም. ግማሽ ሚሊዮን ቶን የነበረው ዓመታዊ የቡና ምርት 2017 ዓም ላይ ወደ 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ቶን የሚጠጋ ምርት ማግኘት በመቻሉ ኢኮኖሚው ላይ ያለውን ከፍ ያለ አስተዋጽኦ ማስቀጠል ችሏል። በመሆኑም፣ የተያዘውን የተቀናጀ የልማት ስትራቴጂ በተግባር በመተርጎም የቡናን ምርት በጥራትና በብዛት ማሳደግ፣ የሀገሪቱን የማክሮ-ኢኮኖሚ መረጋጋት ከመደገፍ ባለፈ የኢትዮጵያን ቡና የወደፊት ጉዞ እና ዓለም አቀፋዊ መሪነት እጅግ አስተማማኝ ያደርገዋል።
በክልሉ ከእንስሳት ሀብት የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ ለእንስሳት ጤና ትኩረት ተሰጥቷል
Aug 13, 2026 287
ጂንካ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከእንስሳት ሀብት የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ ለእንስሳት ጤና ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡ በክልሉ ዲመካ ከተማ ከ446 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ለሚገነባው የዲመካ ክልላዊ የእንስሳት ጤና ላቦራቶሪ ዛሬ የመሰረት ድንጋይ ተቀምጧል። የመሰረት ድንጋዩን ያስቀመጡት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ በክልሉ ከእንስሳት ሀብት የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ ለእንስሳት ጤና ትኩረት ተሰጥቷል፡፡   በክልሉ የእንስሳት እርባታ በተለይ የአርብቶ አደሩ የኑሮ መሰረት በመሆኑ የእንስሳትን ጤና መጠበቅ የአርብቶ አደሩን ሕልውና መጠበቅ መሆኑን ተናግረዋል። ዲመካ ላይ የሚገነባው የእንስሳት ጤና ላቦራቶሪ ከአካባቢው አልፎ ለክልሉም ጥቅም የሚሰጥና ለእንስሳት ጤና መጠበቅ ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አመልክተዋል። የላቦራቶሪ ፕሮጀክቱ ግንባታ በተያዘለት የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ይደረጋል ብለዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ የአርብቶ አደር አደጋ ሥጋት ቅነሳና አካታች የኢኮኖሚ እሴት ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ ዶክተር ስዩም መታፈሪያ በበኩላቸው እንዳሉት፤ የዲመካ ክልላዊ የእንስሳት ጤና ላቦራቶሪ ድንበር ዘለል የእንስሳት በሽታዎችን ለመከላከልና አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል ነው።   ለግንባታው ከ446 ሚሊዮን ብር በላይ መመደቡን ጠቅሰው፣ ላቦራቶሪው በመንግሥት እና በዓለም ባንክ ድጋፍ እንደሚገነባ አስታውቀዋል። ግንባታውን በአንድ ዓመት ከ6 ወር ጊዜ ለማጠናቀቅ መታቀዱን ገልጸው፣ ላቦራቶሪው የእንስሳት በሽታ ምልክቶች ሲኖሩ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት ያስችላል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪ ከዚህ ቀደም በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ወዳሉ ሀገር አቀፍ የእንስሳት ጤና ላቦራቶሪዎች ናሙና በመላክ ሲባክን የነበረውን ጊዜና ገንዘብ ለመቆጠብ ያስችላል ብለዋል።
የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ርብርብ እየተደረገ ነው
Aug 13, 2026 245
ባህርዳር፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ርብርብ ሲደረግ መቆየቱን የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ፡፡ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ለ19 ሺህ 698 የከተማዋ ነዋሪዎች የመኖሪያ ቤት ተጠቃሚ የሚያደርግ ቦታ ለመስጠት የእጣ ማውጣት ስነ ስርአት አካሂዷል።   የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው በስነ ስርአቱ ላይ ባስተላለፉት መልእክት ዜጎችን የመኖሪያ የቤት ባለቤት የማድረግ ጉዳይ ከመንግስት የሰው ተኮር ፕሮጀክት አንዱ ነው።   የባህር ዳር ከተማን እድገት ለማፋጠን ከሚከናወነው የመሠረተ-ልማት ግንባታ ጎን ለጎን የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለመቅረፍ ከፍተኛ ርብርብ ሲደረግ መቆየቱን ተናግረዋል። በዛሬው ዕለትም በመንግሥት የትኩረት አቅጣጫ መሠረት በ901 ማህበራት ለተደራጁ 19 ሺህ 698 ዜጎች የብሎክ ዕጣ ማውጣት መቻሉን አስታውቀዋል። የብሎክ ዕጣ ማውጣት የተቻለው የከተማ አስተዳደሩ ለቤት መስሪያ የሚሆን ቦታ አስፈላጊውን ካሳ በመክፈልና ከሦስተኛ ወገን ነፃ በማድረጉ መሆኑንም አመልክተዋል። ከዚህ ቀደም እስከ 10 ዓመት ድረስ ይቆይ የነበረውን የቤት መስሪያ ቦታ የማቅረብ ሂደት አሁን ላይ በቴክኖሎጂ በመታገዝ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ማቅረብ የሚያስችል አቅም መፈጠሩን ገልጸዋል። ይህም ዜጎች ተረጋግተው ተግባራቸውን እንዲከውኑ ለማድረግ ከማስቻሉም በላይ ከተማዋን ለኑሮ፣ ለንግድና ለኢንቨስትመንት የተመቸች ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። የቤት መስሪያ ቦታው የሚሰጠው በወረብ፣ በአዲስ ዓለም፣ በመኮድና በሰልቸል ሳይቶች መሆኑንም አብራርተዋል።   የቦታው ተጠቃሚ የሚሆኑ ዜጎች ፈጥነው ወደ ግንባታ በመግባት ለወጣቶች የሥራ ዕድል፣ ለራሳቸውም ሀብት እንዲፈጥሩ አቶ ጎሹ አሳስበዋል። በዕጣ ማውጣት ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የከተማ አስተዳደሩ፣ የክልሉ ባለድርሻ አካላት እና የማህበራት ተጠቃሚ አባላት ተገኝተዋል።
በብሄረሰብ አስተዳደሩ ዘግይቶ የጣለውን ዝናብ በማቀብ ለሰብል ልማት ለማዋል ርብርብ እየተደረገ ነው
Aug 13, 2026 145
ሰቆጣ ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ዘግይቶ የጣለውን ዝናብ በማቀብ ለሰብል ልማት ለማዋል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የአስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ገለፀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አብዛኛው በአስተዳደሩ ስር ያሉ አካባቢዎች ዝናብ አጠር በመሆናቸው የዝናብ እጥረቱን በመቋቋም ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሠራ ይገኛል። በዚህም 120 ሺህ 638 ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን በተደረገ ጥረት እስካሁን 80 በመቶ ያህሉን ማሳካት መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ከተዘራው መሬት ውስጥም 57 ሺህ 612 ሄክታሩ ድርቅን የሚቋቋሙና ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን በመለየት ማልማት መቻሉንም አመልክተዋል። አርሶ አደሩ እስከ አሁን ባከናወናቸው ተግባራትም ከ9 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ የእርጥበት እቀባ ሥራ ማከናወኑን ተናግረዋል። ከአካባቢው የአየር ጸባይ መለዋወጥና የዝናብ መቆራረጥ ጋር ተያይዞ ሊከሰት የሚችል ተባይን ለመከላከል ግብረ-ኃይል ተቋቁሞ ወደ ሥራ መግባቱን ጠቁመዋል። አርሶ አደሩ የእርጥበት እቀባውን አጠናክሮ እንዲቀጥልና ሰብሉን ከተባይና ከአረም እንዲከላከል የግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራ እየተሠራ እንደሚገኝም አስረድተዋል። የጋዝጊብላ ወረዳ 06 ቀበሌ ነዋሪዎቹ አርሶ አደር እምወደው አየለ እና አርሶ አደር ደስታነህ ንጉሡ በበኩላቸው፤ የዝናብ እጥረቱን ለመቋቋም በእርሻቸው ላይ ውሃ የሚያቁሩ ጉድጓዶችን መቆፈራቸውን ተናግረዋል። ከባለሙያ የሚሰጣቸውን ምክረ-ሐሳብ መሠረት በማድረግ ሰብላቸውን በወቅቱ ዘርተው አሁን ላይ ወደ አረም ሥራ መግባታቸውንም ገልጸዋል። በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በ2018/2019 የመኽር እርሻ ወቅት 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በሰሜን ሸዋ ዞን በማዕድን ሀብት ልማት አበረታች ውጤት እየተመዘገበ ነው
Aug 13, 2026 121
ደብረ ብርሃን፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በሰሜን ሸዋ ዞን የማዕድን ሀብትን አልምቶ ጥቅም ላይ በማዋል አበረታች ውጤት እየተመዘገበ መምጣቱን የዞኑ የማዕድን ሀብት ልማት መምሪያ ገለጸ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ታደሰ በቀለ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እንዳሉት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የባህላዊ ማዕድናት ምርትና ግብይት ሕጋዊ መስመር ተከትሎ እንዲከናወን ተደርጓል። በዚህም 7 ነጥብ 7 ሚሊዮን ቶን ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ ማቅረብ እንደተቻለ ነው ያመለከቱት። የኢንዱስትሪ፣ የኮንስትራክሽንና የከበሩ ማዕድናት በጥራት ተመርተው ለገበያ ማቅረብ በመቻሉም ከ4 ነጥብ 4 ሚሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ማዳን እንደተቻለ ገልጸዋል። ከዚህም ባለፈ በአካባቢው ጂፕሰም፣ ላይምስቶንና ኦፓልን ጨምሮ ከ27 በላይ የከበሩና የኢንዱስትሪ ማዕድናት መኖራቸውን ጥናት ማረጋገጥ መቻሉን ተናግረዋል። በቀጣይም ዘርፉን በዘመናዊ መንገድ ለመምራትና የግብይት እሴትን ለማጠናከር በጣርማበር ወረዳ የከበሩ ማዕድናት መግዣና መሸጫ የገበያ ማዕከል እየተገነባ ይገኛል ብለዋል። የአካባቢውን ማህበረሰብ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለማድረግና የስራ ዕድል ለመፍጠር በግል እና በኢንተርፕራይዝ ለተደራጁ 247 ባህላዊ ማዕድን አምራች ማህበራት የስራ ፈቃድ መሰጠቱንም አክለው ገልጸዋል። በእንሳሮ ወረዳ የ"ሽመልስ ማሞ እና ጓደኞቻቸው" ህብረት ሽርክና ማህበር ሰብሳቢ አቶ ሽመልስ ማሞ በበኩላቸው፤ ማህበሩ ለግንባታ አገልግሎት የሚውል ማዕድን አምርቶ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆኑን ተናግረዋል። ማህበሩ 47 አባላት ያሉት ሲሆን፣ የማዕድን ሀብቱን አምርቶ ከሚገኘው ሽያጭ አባላቱን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። በመርሐቤቴ ወረዳ ቁም አምባ ቀበሌ “ሲልካ“ የተባለ ለጠርሙስ ምርት በግብዓትነት የሚያገለግል ማዕድን እሴት ጨምረው በማቅረብ ተጠቃሚ እንደሆኑ የገለጹት ደግሞ የ"ማክን ትሬዲንግ" ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ ሙሉጌታ ደምሴ ናቸው። ድርጅታቸው አሁን ላይ ከ100 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፍጠሩን ጠቅሰው፤ በቀጣይም ምርታቸውን በተሻለ ፍጥነትና ጥራት ለገበያ ለማቅረብ እየሰሩ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
በክልሉ ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ወደ ሥራ ገብተዋል
Aug 13, 2026 270
ሚዛን አማን፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በ2018 በጀት ዓመት ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች ፈቃድ ወስደው ወደ ሥራ መግባታቸውን የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ምክትልና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ከበደ ተስፋዬ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ክልሉ ለኢንቨስትመንት ሥራ ያለውን አቅም በሚገባ ለመጠቀም በተሰጠው ትኩረት ውጤት እየተገኘ ነው። በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሀብቶች በግብርና፣ በአገልግሎት እና በኢንዱስትሪ ዘርፍ ለመሰማራት ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት ፈቃድ መሰጠቱን ተናግረዋል።   ፈቃድ ከተሰጣቸው 123 ባለሀብቶች መካከል 63ቱ በግብርና ዘርፍ መዋለንዋያቸውን ለማፍሰስ ፈቃድ የወሰዱ ሲሆን ይህም የክልሉን ጸጋ መሠረት ያደረገ መሆኑን አመልክተዋል። በአገልግሎት ዘርፍ በከተሞች የተሻለ ለውጥ እየተመዘገበ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ከበደ፣ በኢንዱስትሪ ዘርፍ ያለውን ውስንነት ለመሙላት የሚያስችል የተቀናጀ እንቅስቃሴ መጀመሩን ጠቁመዋል። በበጀት ዓመቱ ወደሥራ ለገቡ ባለሀብቶች ከ16 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት እንደተላለፈና ከ110 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩንም ተናግረዋል።   ለባለሀብቶቹ የሥራ ፈቃድ ከመስጠት ባሻገር ለልማት ፕሮጀክቶቻቸው ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግ የተናገሩት ኃላፊው በትላልቅ የኢንዱስትሪ ዘርፎች ለሚሠማሩ ባለሀብቶች ክልሉ ልዩ ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። በክልሉ ሚዛን አማን ከተማ በሆቴልና ቱሪዝም ኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ዋለልኝ ቸርነት በበኩላቸው፤ መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ወደ ተግባር መግባታቸውን ገልጸዋል።   አካባቢው ከፍተኛ የንግድ እና ሌሎች ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ያለበት መሆኑ ለኢንቨስትመንት ሥራ ውጤታማነት የራሱን አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በከተማ አስተዳደሩ በኩል የተደረገላቸው የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ሥራቸውን በተሻለ ሁኔታ ለማከናወን አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ጠቁመዋል። መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ የሰጠው ትኩረት በየመስኩ ኢኮኖሚው እንዲነቃቃ አድርጓል ያሉት ደግሞ በግንባታ ሥራ የተሰማሩት አቶ አንድነት ሀብተማርያም ናቸው።   በተለይ በከተሞች በአገልግሎት መስጫ ኢንቨስትመንቶች ላይ እየመጣ ያለውን ለውጥ ተከትሎ የመብራት፣ የመንገድ፣ የውሃና ሌሎች መሠረተ ልማቶች አብረው እየተስፋፉ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ለተሰማሩበት የግንባታ ዘርፍ ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር ባሻገር ለከተሞች መስፋፋትና ለአካባቢው ዕድገት በጎ አሻራ ያሳርፋል ብለዋል፡፡
በሐረሪ ክልል የኢንቨስትመንት ፍቃድ እና መሬት ወስደው ወደ ግንባታና ማምረት ባልገቡ 12  ባለሀብቶች ላይ  እርምጃ ተወሰደ
Aug 13, 2026 97
ሐረሪ ፤ነሐሴ 7/2018 (ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል የኢንቨስትመንት ፍቃድ እና መሬት ወስደው ወደ ግንባታና ማምረት ባልገቡ 12 ባለሀብቶች ላይ የኢንቨስትመንት ፍቃድ ስረዛና እገዳ እርምጃ መወሰዱን የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሀምዲ ሰለሃዲን ለኢዜአ እንዳሉት የክልሉ መንግሥት በኢንቨስትመንት ተሰማርተው ለሚገኙና አዳዲስ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች ምቹ ሁኔታን እየፈጠረ ይገኛል። ከዚህም ባለፈ የባለሀብቶች እንቅስቃሴ ያለበትን ሁኔታ የመስክ ምልከታ በማከናወን በገቡት ውል መሰረት ወደ ስራ ያልገቡ ባለሃብቶች ላይ እርምጃ እየወሰደ እንደሚገኝም ገልጸዋል።   ባለሀብቱ ከመንግስት የኢንቨስትመንት ፈቃድና መሬት የሚወስደው የክልሉን ልማት ለማፋጠን በመሆኑ የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባም ነው ያሳሰቡት። በዚህም በክልሉ በኢንቨስትመንት አዋጅ፣ ደንብና መመሪያ መሠረት ቀደም ሲል የኢንቨስትመንት ፈቃድና መሬት ወስደው ወደስራ ያልገቡና ግንባታ ያጓተቱ 3 ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰረዙን ተናግረዋል። እንዲሁም መሬት ወስደው በውሉ መሠረት ወደ ግንባታ ሥራ ባልገቡና የሼድ ግንባታ አጠናቀው ወደ ማምረት ባልገቡ 9 ባለሀብቶች ላይ ደግሞ ፈቃድ የማገድ እርምጃ መውሰዱን አስታውቀዋል። ከዚህ በተጨማሪም የኢንቨስትመንት ፈቃድና መሬት ወስደው አዝጋሚ የግንባታ ሂደት ውስጥ ለሚገኙ 7 ባለሀብቶችም የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ተሰጥቷል ብለዋል። በባለሀብቶቹ ላይ ከሚወሰደው እርምጃ ጎን ለጎንም ባለሀብቶቹ የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች የመፍታት ሥራ ተከናውኗል ሲሉ ተናግረዋል። በባለሀብቶቹ ላይ እርምጃ መወሰድ መጀመሩም የሌሎች ፕሮጀክቶች ግንባታ ሥራዎች እንዲፋጠኑ ዕድል መፍጠሩን ጠቁመው በቀጣይም መሰል እርምጃዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አመልክተዋል።   በቀጣይም ባለሀብቶቹ ወደ ሥራ ካልገቡ ፈቃድ በመሰረዝ የወሰዱት መሬት ለመሬት ባንክ ገቢ እንደሚደረግ አስታውቀዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ ከ3 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ላስመዘገቡ 96 ባለሀብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መሰጠቱን ጠቅሰዋል። ለባለሀብቶቹም የኢንቨስትመንት ፈቃድ የተሰጣቸው በማኑፋክቸሪንግ፣ ሆቴል፣ ግብርና፣ በገበያ ማዕከልና በሌሎች ዘርፎች ለመሰማራት ጥያቄ በማቅረባቸው መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም