ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ፈተናዎችን ወደ ዕድል የቀየረው የለውጡ ዓመታት የኢንዱስትሪው ዘርፍ እመርታ
Jul 21, 2026 51
በሙሴ መለሰ ካለፉት ጥቂት ዓመታት ወዲህ በኢትዮጵያ የተከናወኑ ሁለንተናዊ የፖሊሲና የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች በኢንዱስትሪው ዘርፍ ላይ አዲስ መነቃቃትንና ተጨባጭ ስኬቶችን አስመዝግበዋል።መንግስት የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳን ቀርፆ ወደ ተግባር በመግባት፣ የግል ዘርፉን በማበረታታት እና የአምራች ኢንዱስትሪውን በማዘመን ረገድ ከፍተኛ ውጤት አስመዝግቧል። ይህ መዋቅራዊ ሽግግር የሀገሪቱን የገቢና ወጪ ንግድ ከማመጣጠን ባለፈ፣ በሁሉም ንዑሳን የኢንዱስትሪ ዘርፎች ላይ ተስፋ እንዲፈነጥቅ አድርጓል። የለውጡ ዓመታት የኢንዱስትሪ ስኬቶች መካከል በዋንኛነት የሚጠቀሰው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሚያዚያ ወር 2014 ዓ.ም ይፋ የተደረገው የ “ኢትዮጵያ ታምርት” ሀገራዊ ንቅናቄ ነው። ይህ ንቅናቄ በፋይናንስ፣ በግብዓት እና በኃይል አቅርቦት እጥረት ምክንያት ተዘግተው የነበሩ አምራች ኢንዱስትሪዎችና ፋብሪካዎችን ዳግም ወደ ሙሉ ማምረት አቅማቸው እንዲመለሱ አድርጓል። ንቅናቄው በተጀመረባቸው የመጀመሪያዎቹ ተከታታይ ዓመታት ብቻ የአገር ውስጥ ምርትን በማሳደግ በርካታ የውጭ ምንዛሬ የሚያስወጡ የውጭ ምርቶችን በአገር ውስጥ ለመተካት የተቻለ ሲሆን፣በተለይም በጨርቃ ጨርቅ፣በቆዳና የቆዳ ውጤቶች፣ እንዲሁም በምግብና መጠጥ ኢንዱስትሪዎች ላይ ከፍተኛ የምርት ዕድገት ተመዝግቧል። ይህም የሀገሪቱን የአምራች ኢንዱስትሪ አማካይ የማምረት አቅም በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደጉን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሚያዚያ ወር 2018 ዓ.ም ከኢቢሲ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፣ኢትዮጵያ ያጋጠሟትን እንደ ኮሮና ወረርሽኝና የአጎዋ (AGOA) ስረዛ ያሉ ዓለም አቀፋዊ ጫናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር በዘርፉ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት ችላለች። የኢንዱስትሪ መሪነቱን ከመንግሥት ወደ ግሉ ዘርፍ የማሸጋገር ሥራን ጨምሮ በተቀረጹ ስትራቴጂካዊ ምሰሶዎች አማካኝነት፣ ቀደም ሲል 8 ሺህ ገደማ የነበሩት አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች በአሁኑ ወቅት ከ26 ሺህ በላይ መድረሳቸውን አመልክተዋል። በተጨማሪም በተለያዩ ማነቆዎች ሥራ አቁመው የነበሩ 800 ገደማ ፋብሪካዎች አስፈላጊው ድጋፍ ተደርጎላቸው ወደ ማምረት መመለሳቸውንና ይህም የኢንዱስትሪዎችን አማካይ የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማድረጉን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል። ተኪ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በማምረት ሂደትም እስካሁን ለውጭ ምርት ይወጣ የነበረውን 3.6 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማዳን መቻሉን ገልጸዋል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያን የማኑፋክቸሪንግ ማዕከል ለማድረግ በሎጂስቲክስና በቴክኖሎጂ ዘርፍ ታላላቅ ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ መሆኑን በወቅቱ ገልጸው ነበር። የኢትዮጵያን ግብርና ከኢንዱስትሪ ጋር ለማስተሳሰር የተከናወኑት ተግባራት ሌላኛው የለውጡ ማሳያ ነው። በይርጋለም፣ቡሬ እና ቡልቡላ የሚገኙ የተቀናጁ የግብርና ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ወደ ሙሉ ስራ መግባት አርሶ አደሩ ምርቱን በቀጥታ ለፋብሪካዎች እንዲያቀርብና እሴት የተጨመረበት ምርት ለውጭ ገበያ እንዲቀርብ መንገድ ከፍቷል። ይህ ስትራቴጂ የገጠር የስራ ዕድል ፈጠራን ከማሳደጉም በላይ የኢንዱስትሪዎቹን የጥሬ ዕቃ ጥገኝነት ሙሉ በሙሉ በአገር ውስጥ ምርት ለመተካት ትልቅ እገዛ አድርጓል።ከዚሁ ጋር ተያይዞ በኬሚካል፣ በፋርማሲዩቲካል እና በሕክምና መገልገያ ቁሳቁሶች ማምረቻ ዘርፍ የታየው ስኬት ለሀገሪቱ የጤና ዋስትና ትልቅ ምሰሶ ሆኗል። ከዚህ ቀደም አብዛኛው የመድኃኒት ፍላጎት በከፍተኛ ወጪ ከውጭ የሚገባ ሲሆን፣ በለውጡ ዓመታት ግን የአገር ውስጥ መድኃኒት አምራቾች አቅም እንዲጎለብትና አዳዲስ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ የፋርማሲዩቲካል ፋብሪካዎች ወደ ማምረት እንዲገቡ ተደርጓል። ይህም ለአገር ውስጥ ገበያ ጥራት ያላቸው መድኃኒቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ አስችሏል። በሌላ በኩል፣በኮንስትራክሽን እና ማዕድን ኢንዱስትሪ ላይ የታየው መነቃቃት የሀገሪቱን የመሠረተ ልማት ፍላጎት በራስ አቅም ለመደገፍ አስችሏል። አዳዲስ የሲሚንቶ እና የብረት ፋብሪካዎች ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉ እና ነባሮቹ አቅማቸውን እንዲያሳድጉ መደገፉ፣ በሀገሪቱ ለሚታዩት ሰፊ የኮሪደር ልማት እና የዘመናዊ ከተሞች ግንባታ ፕሮጀክቶች የአገር ውስጥ ግብዓትን በበቂ ሁኔታ ለመጠቀም አስችሏል። ማዕድናትን በተመለከተም፣ ጥሬ ግብአት ከመላክ ይልቅ እሴት ጨምሮ የመላክ ፖሊሲ በመተግበሩ የዘርፉን የሀገር ውስጥ ገቢ ድርሻ በከፍተኛ ሁኔታ አሳድጎታል። ለኢንዱስትሪው ዘርፍ መፋጠን ሌላው ዋነኛ አስደጋፊ የሆነው የኢነርጂ እና ታዳሽ ኃይል ልማት ዘርፍ ነው። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ጨምሮ ሌሎች የውሃ፣ የንፋስ እና የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች ግንባታ መጠናቀቅና ወደ ሥራ መግባት አምራች ኢንዱስትሪዎች የሚያገኙትን የኃይል አቅርቦት እንዲያድግ አስችሏል። ይህ የአረንጓዴ የኃይል አቅርቦት የፋብሪካዎችን የማምረት አቅም ከማሳደጉም በላይ፣ የኢትዮጵያን ምርቶች በዓለም አቀፍ ገበያ ለአካባቢ ጥበቃ ተስማሚ (Eco-friendly) እንዲሆኑ አድርጓል። ከነዚህ ዘርፎች ባሻገር፣ኢትዮጵያ ወደ ዲጂታል ኢኮኖሚ የምታደርገውን ሽግግር ተከትሎ በቴክኖሎጂው እና በአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ አበረታች ስኬቶች ተመዝግበዋል። በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች፣ የሞባይል ስልኮች እና የቤት ውስጥ መገልገያ ቁሳቁሶች የመገጣጠም ስራ በስፋት እየተከናወነ ይገኛል።በተለይም ደግሞ ለአካባቢ ጥበቃና ለነዳጅ ወጪ ቅነሳ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያላቸው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች (EVs) በአገር ውስጥ በስፋት መገጣጠም መጀመራቸው ሀገሪቱ በቴክኖሎጂ ራሷን እንድትችል እና ለሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶች ዘላቂ የስራ ዕድል እንዲፈጠር መሰረት የጣለ እርምጃ ሆኗል። በአጠቃላይ፣ የለውጡ ዓመታት በኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ውስጥ መዋቅራዊ ሽግግር የተደረገባቸው ነበሩ ሊባል ይችላል። ከፖሊሲ ማሻሻያ ጀምሮ እስከ መሬት ወርደው የተተገበሩ ሀገራዊ ንቅናቄዎች ድረስ የተከናወኑት ተግባራት ሀገሪቱ በምርት ራሷን እንድትችል እና የውጭ ምርት ጥገኝነትን እንድትቀንስ አግዘዋታል። እነዚህ የተመዘገቡ ስኬቶች የኢትዮጵያን የነገ ብልጽግና የሚያረጋግጡ ጠንካራ መሰረቶች ናቸው።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት በተካሄዱ የልማት ስራዎች ተጠቃሚ ሆነናል
Jul 21, 2026 32
ከሚሴ፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፡-ባለፉት የለውጥ ዓመታት ተግባራዊ በተደረጉ የልማት ስራዎች ተጠቃሚ መሆናቸውን በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን ነዋሪዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት በከሚሴ ከተማ "የኢትዮጵያ ከተሞች የኮሪደር ልማት" በሚል መሪ ሃሳብ ያዘጋጀው ስለ ኢትዮጵያ የተሰኝ የምክክር መድረክ ተካሂዷል።   በምክክር መድረኩ ላይ የተገኙት የከሚሴ ከተማ ነዋሪ ሼህ የሱፍ ይማም እንደገለፁት፣ በለውጡ ዓመታት በተቀናጀ መንገድ ሰላምን ከማስፈን ባሻገር ተግባራዊ በተደረጉ የልማት ስራዎች ተጠቃሚ ሆነናል። ከለውጡ በፊት ከተማዋ በልማት ወደ ኋላ የቀረች ከመሆኑ በተጨማሪ ግጭቶች የሚታዩባት እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ላይ የተሟላ ሰላም ከመሰፈኑ ባሻገር በከተማዋ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች መሰረተ ልማቶች መሟላታቸው ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል።   ሌላው የውይይቱ ተሳታፊ የባቲ ከተማ ነዋሪ አቶ ኡመር መሐመድ በበኩላቸው፣ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የሚሰሩ የልማት ስራዎች ማሕበረሰቡ ለረዥም ጊዜ ሲያነሳቸው ለነበሩ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ ናቸው። በተለይም የአካባቢውን ሰላም ከማጽናት ባለፈ የዲጂታል አገልግሎት በተሻለ ጥራት ተደራሽ በማድረግ የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል። የአካባቢያችን ሰላም ተጠብቆ በተሰሩ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ተጠቃሚ ሆነናል ያሉት ደግሞ የጨፋ ሮቢት ከተማ ነዋሪ አቶ አሊ ሰይድ ናቸው።   ባለፉት የለውጥ ዓመታት ከአጎራባች ዞኖችና ክልሎች ጋር ያለንን ግንኙነት በማጠናከር በልማት ጭምር መተሳሰሩ ይበልጥ እንድንቀራረብና በጋራ ተጠቃሚ መሆን እንድችል አድርጓል ነው ያሉት። የኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አህመድ አሊ በበኩላቸው፣ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ህብረተሰቡን በማሳተፍ ሰላምን ለማስፈን በተከናወኑ ተግባራት ውጤት ተመዝግቧል ነው ያሉት ። ከሰላም ማስክበር ስራው በተጓዳኝ የህዝቡን የልማት ጥያቄ መሰረት ያደረጉ የልማት ስራዎችን በማከናወን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ እንደተቻለ ገልፀዋል።   በመድረኩ የከተማና መሰረት ልማት ሚኒስትር ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒን ጨምሮ የፌዴራል ፣ የክልል ፣ የዞንና የከተማ አመራሮችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በዞኑ ህብረተሰቡን በቅርበት ለማገልገል ወደ ተግባር የገቡ የቀበሌ አደረጃጀቶች ለልማት ስራዎች ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል
Jul 21, 2026 36
ጊምቢ፣ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፡-በምዕራብ ወለጋ ዞን ህብረተሰቡን በቅርበት ለማገልገል ወደ ተግባር የገቡ የቀበሌ አደረጃጀቶች የተሟላ አገልግሎት ከመስጠት ባለፈ ለልማት ስራዎች ምቹ ሁኔታ እንደፈጠሩላቸው ነዋሪዎች ገለጹ። አደረጃጀቱ በቅርበት የተሻለ አገልግሎት እንዲያገኙ ከማስቻሉም በላይ፣ ተጠቃሚነታቸውን የሚያሳድጉ የተለያዩ የልማት ስራዎች እንዲከናወኑ ምቹ ሁኔታን እየፈጠረ እንደሚገኝ የዞኑ ነዋሪዎች ገልፀዋል፡፡ አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት ነዋሪዎች መካከል የጊምቢ ከተማ 01 ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ አስካለ ሕርጳ፤ የቀበሌ አደረጃጀቱ የመንግሥት አገልግሎትን በቅርበት ከማግኘታቸው በላይ በአካባቢያቸው የተለያዩ የልማት ስራዎች እንዲከናወኑ አስችሏል፡፡ በተለይም አደረጃጀቱ ተግባራዊ ከተደረገ ወዲህ በአካባቢያቸው የነበረውን የጸጥታ ችግር መቅረፍ መቻሉን ጠቅሰው፤ አመራሮቹ በየጊዜው ከህብረተሰቡ ጋር በመቀራረብ ይስተዋሉ የነበሩ የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዲፈቱ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። የመንዲ ከተማ የቀርሳ ዋልጋ ቀበሌ ነዋሪ አቶ በላይ መልካሙ በበኩላቸው፣ የተዘረጋው አደረጃጀት ተጠቃሚነታቸውን ያሳደጉ የተለያዩ የልማት ስራዎች እንዲከናወኑ ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ብለዋል። በተለይም በአካባቢያቸው ሰላም እንዲሰፍን ከማድረጉም በላይ የቆዩ የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዲቀረፉ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስረድተዋል። አሁን የተዘረጋው የቀበሌ አደረጃጀት ጉዳያቸውን ለማስፈጸም ወደተለያዩ የመንግስት መስሪያ ቤቶች ከማመልከትና ከመንገላታት እንደታደጋቸው የተናገሩት ደግሞ አቶ አያና ገላልቻ ናቸው። ከዚህ ቀደም ከመሬት ወሰን ይዞታ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን ለማስፈጸም ለተለያዩ እንግልቶች ይዳረጉ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ግን በአዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት ጉዳያቸውን በአጭር ጊዜ ማስፈጸም መቻላቸውን ጠቅሰዋል። አደረጃጀቱ በስራ ላይ መዋሉ ውስብስብ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመፍታትና ሠላም እንዲሰፍን በማድረግ በኩል አዎንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም አክለው ገልጸዋል። የቀበሌ አደረጃጀቱ ቀልጣፋ፣ ዘመናዊ እና ተደራሽ የሆነ አገልግሎት ለህብረተሰቡ በቅርበት መስጠት ማስቻሉን የተናገሩት ደግሞ የጊምቢ ከተማ 01 ቀበሌ አስተዳዳሪ አቶ ሙሊጌታ አደሙ ናቸው። በአደረጃጀቱ ህብረተሰቡን በማቀናጀት በአካባቢው የነበረውን የጸጥታ ችግር በመቅረፍ ሰላም እንዲሰፍን ተድርጓል ብለዋል። በቀጣይም የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመለየትና ተደራሽ የሆኑ አገልግሎቶችን በማሳለጥ የህዝብ ጥያቄዎችን አግባብ ባለው መንገድ ለመፍታት በተቀናጀ መልኩ እንደሚሰራ አመላክተዋል።   የምዕራብ ወለጋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ተሊላ ተረፋ እንደተናገሩት በዞኑ 464 የቀበሌ አደረጃጀቶች ተደራጅተው ለሕዝቡ በቅርበት አገልግሎት እየሰጡ ይገኛል። አደረጃጀቱ በተለይም በዞኑ ይስተዋሉ የነበሩ የፀጥታ ችግሮችን በመቅረፍ ሂደት ህብረተሰቡ ከጸጥታ አካላት ጋር እንዲሰራ እድል ፈጥሯል ብለዋል። ይህ ብቻ ሳይሆን የዞኑ ህዝብ ለረጅም ጊዜ ሲያነሳቸው የነበሩ የመሰረተ ልማት ጥያቄዎችን ፈጥኖ ለመመለስ እድል መፍጠሩንም አስረድተዋል።  
በጅማ ዞን የሩዝ ምርታማነት እያደገ መጥቷል
Jul 21, 2026 82
ጅማ፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፦ በጅማ ዞን የሩዝ ሰብልን ለማስፋፋት በተከናወነው ሥራ ምርታማነቱ እያደገ መምጣቱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገልጿል። በዞኑ በ2018/19 የምርት ዘመን 393 ሺህ 600 ሄክታር መሬት በሩዝ ሰብል ለመሸፈን ታቅዶ እስካሁን ከ370 ሺህ ሄክታር በላይ የመሬት ዝግጅት መደረጉን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሚፍታህ ጋሊ ተናግረዋል። በዞኑ 19 ወረዳዎች ሩዝ የሚለማ መሆኑን የገለጹት አቶ ሚፍታህ ባለፈው የምርት ዘመን ከ14 ሚሊዮን 800 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪም ምርታማነቱን ለማስፋፋት ምርጥ ዘር የማባዛት ሥራ እየተከናወነ ሲሆን በዞኑ በሚገኙ የኅብረት ሥራ ዩኒየኖች አማካይነት ስኬታማ ሥራ መከናወኑን ተናግረዋል። በዘንድሮ ዓመት በጅማ ዞን ቀርሳ ወረዳ የኅብረት ሥራ ዩኒየን በኩል 50 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ምርጥ ዘር ተባዝቶ በቴክኖሎጂ በመታገዝ ያለ ብክነት ተሰብስቧል ነው ያሉት። ይህም ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባውን የሩዝ ሰብል ምርጥ ዘር በሀገር ውስጥ ለማምረት ታቅዶ እየተሠራ በመሆኑ ነው ብለዋል።   ከዚህ በተጨማሪም በሩዝ ሰብል ልማት ላይ ለበርካቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሮ ተጠቃሚ እየሆኑ ነው ብለዋል። በጅማ ዞን ቀርሳ ወረዳ በኅብረት ሥራ ዩኒየን በዘር ማባዛት ሥራ ላይ ተሰማርተው ባገኙት የሥራ ዕድል ውጤታማ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ ሲራጅ ጀማል እና ዛኪር አባራያ ናቸው። ዞኑ ምቹ የአየር ጠባይ ያለው እንደመሆኑ በየጊዜው የተሻለ ምርት እየተሰበሰበ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህ ሥራ ላይ ከተሰማሩ በኋላ ሕይወታቸው እየተሻሻለ መሆኑን ገልጸው ከዚህ በተጨማሪም ባላቸው መሬት ላይ በማምረት ተጠቃሚ መሆናቸውን አክለዋል። ወጣት ከድር አባዝናብ፤ ዩኒየኑ የሩዝ ሰብል ምርጥ ዘርን ለማስፋፋት እያከናወነ በሚገኘው የግብርና ሥራ ተሰማርቶ ከራሱ አልፎ ቤተሰቡን እያገዘ መሆኑን ጠቅሷል።
የተፈጥሮ ሀብትና የዱር እንስሳት ጥበቃ ሥራዎች ለቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት ያላቸውን አስተዋጽኦ ይበልጥ የሚያልቁ ተግባራት ይጠናከራሉ
Jul 21, 2026 103
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፦ የተፈጥሮ ሀብትና የዱር እንስሳት ጥበቃ ሥራዎች ለቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት ያላቸውን አስተዋጽኦ ይበልጥ የሚያጎሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን 60ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን እያከበረ ይገኛል፡፡ በበዓሉ ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች፣ የዓለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።   የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር) በመድረኩ እንደገለጹት፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመሩት የገበታ ለሀገር፣ የገበታ ለሸገር እና የገበታ ለትውልድ ፕሮጀክቶች ለቱሪዝም ዘርፉ አዳዲስ ምዕራፎች መክፈታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት ለተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ በተሰጠው ልዩ ትኩረት የዱር እንስሳት እንዲመለሱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን አብራርተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ተግባራዊ በመደረግ ላይ የሚገኘው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ ላይ ትውልዱ አደራውን በሚገባ እንዲወጣ ማስቻሉን ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ በልዩ ልዩ የዱር እንስሳት፣ በብርቅዬ የተፈጥሮ ሀብቶችና በውብ ስነ-ምዳሮች የበለፀገች ሀገር መሆኗን ጠቅሰው፤ እነዚህን ጸጋዎች ጠብቆ ለመጪው ትውልድ ማስተላለፍ የሁሉም የጋራ አደራ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለተፈጥሮ ሀብት እና ለዱር እንስሳት ጥበቃ በሰጠችው ከፍተኛ ትኩረት የሀገሪቱን የደን ሽፋን ማሳደግ መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡ የቱሪዝም እድገት ከተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ጋር በእጅጉ የተቆራኘ በመሆኑ፣ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የተፈጥሮ ሀብትና የዱር እንስሳት ጥበቃ ሥራዎችን አጠናክሮ ለመቀጠል ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል፡፡ ባለፉት 60 ዓመታት የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ጉዞ በብዙ ውጣ ውረዶች ያለፈ መሆኑን ጠቅሰው ለዘርፉ ዕድገትና ለዱር እንስሳት ጥበቃ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ሁሉ ምስጋና አቅርበዋል፡፡
በምእራብ ጎንደር ዞን ከ22 ሺህ 500 በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል
Jul 21, 2026 95
ገንዳውኃ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ22 ሺህ 500 በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን የዞኑ ሥራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። ​የመምሪያ ኃላፊ አቶ ኤፍሬም ወርቁ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የወጣቶችን የሥራ አጥነት ችግር በማቃለል በኢኮኖሚ ራሳቸውን እንዲችሉ የማድረግ ስራ ተሰርቷል። ​በዚህም በበጀት ዓመቱ በዞኑ የሚገኙ ጸጋዎችን በመለየት ከ22 ሺህ 500 በላይ ወጣቶች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልጸዋል። የስራ እድል የተፈጠረላቸው ዜጎች በኮንስትራክሽን፣ በእንጨትና ብረታ ብረት ስራ፣ በአገልግሎት ፣ በከብት ማድለብ፣ በወተት ልማትና ንብ ማነብን ጨምሮ በሌሎች የግብርና ዘርፎች መሰማራታቸውን ገልፀዋል። የስራ እድሉ የተፈጠረላቸው ዜጎች 267 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ የመስሪያ ካፒታል በብድር እንዲያገኙ ከማድረግ ባለፈም ለማምረቻና ለመሸጫ የሚሆኑ ከ700 በላይ ሼዶችና ኮንቲነሮችን ማስረከብ መቻሉን አስረድተዋል። በቀጣይም የዞኑን እምቅ ጸጋዎች በሚገባ ለይቶ በመጠቀም ለወጣቱ የተሻለ የሥራ ዕድል ለመፍጠር በቁርጠኝነት እንደሚሠራ አስገንዝበዋል። ​በዞኑ በከብት ማድለብ ስራ የተሰማራው ወጣት ይስማው አቡዬ ፤በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተመቻቸለት የከብት ማድለብ ሥራ ከ300 ሺህ ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘት መቻሉን ነው የተናገረው። በዚህም ከራሱ አልፎ ቤተሰቦቹን ለመደገፍ እንደቻለ አመልክቶ ስራውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጿል። በዘላቂ ተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ በእጣንና ሙጫ ማምረት ስራ የተሰማራው ወጣት አይሸሽም አለሙ በበኩሉ፤ ከ100 ባለይ ሆነው በመደራጀት በዘርፉ ባገኙት የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጿል። በበጀት ዓመቱ እጣንና ሙጫ በማምረትና ለገበያ በማቅረብ እያንዳንዳቸው ከ200 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ነው ያስታወቀው። በአሁኑ ወቅትም የተፈጥሮ ደኑ እንዲጠበቅ በጋራ ሆነው እየሰሩ መሆኑንም አመልክቷል።
ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፎች ትክክለኛ የልማት ጎዳና ላይ ትገኛለች - አምባሳደሮች
Jul 21, 2026 107
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፦ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፎች ትክክለኛ የልማት ጎዳና ላይ እንደምትገኝ በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር እና የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁት የኦስትሪያ አምባሳደር ገለጹ። ኢትዮጵያ ተግባራዊ ያደረገችው የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠር መቻሉንም ጠቅሰዋል፡፡ በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ የምትከተላቸው የኢኮኖሚ ፖሊሲዎች ዓለም አቀፍ ትኩረት እየሳቡ መሆናቸውን ገልጸዋል። አምባሳደሩ ኢትዮጵያ ማክሮ ኢኮኖሚያዊ ማሻሻያን እየተገበረች እና ዲጂታል ሥርዓትን እያስፋፋች መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ለሀገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለኢኮኖሚያዊ ሽግግር እና ከዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ሥርዓት ጋር ለመቀናጀት እጅግ ጠቃሚ መሆኑን ተናግረዋል። በርካታ የእስራኤል ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ማክሮ ኢኮኖሚያዊ ፖሊሲና በዲጂታል ሥርዓት እየተሳቡ እንደሚገኙ የገለጹት አምባሳደሩ፤ ኢትዮጵያ በኃይል፣ በውሃ እና በሌሎችም ቁልፍ ዘርፎች ባላት ፖሊሲ ትክክለኛ የልማት አቅጣጫዎች ላይ እየተጓዘች መሆኑን አረጋግጠዋል። የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት ተደራሽነት ማስፋፋትን ጨምሮ ኢትዮጵያ በኃይል አቅርቦት እያሳየች ያለው እመርታዊ ለውጥ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ላይ ያላቸውን እምነት የሚያጠናክር መሆኑንም ተናግረዋል። ሀገራቱ በግብርና፣ በጤና፣ በፈጠራና ቴክኖሎጂ፣ በትምህርት እና በምርምር ዘርፎች ላይ የጋራ ፕሮጀክቶችን ተግባራዊ በማድረግ ውጤታማ ሥራዎችን ማከናወናቸውን አብራርተዋል። በማህበራዊና ሕዝብ ለሕዝብ ዲፕሎማሲ ረገድም ሀገራቱ ጠንካራ ትብብር እንዳላቸው ያነሱት አምባሳደሩ፤ በጤና፣ በባህል ልውውጥ፣ በንግድ ትስስር እና በቱሪዝም ዙሪያ ያላቸውን ግንኙነት በማሳያነት አንስተዋል። እስራኤል ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ሁለንተናዊ ትብብር ይበልጥ ለማስፋት ቁርጠኛ መሆኗንም አረጋግጠዋል። የእስራኤል ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ያሉ የኢንቨስትመንት አማራጮችን እያጠኑ መሆኑን አመልክተው፤ በተለይም በጠብታ መስኖ፣ በሰብል ምርት፣ በአቮካዶ፣ ስንዴ፣ ዓሣ እና የዶሮ እርባታ ባሉ የግብርና ዘርፎች ላይ ለመሰማራት ፍላጎት ማሳየታቸውን ተናግረዋል። የሥራ ዘመናቸውን ያጠናቀቁት በኢትዮጵያ የኦስትሪያ አምባሳደር ሲሞን ክናፕ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ሪፎርም የኦስትሪያ ባለሀብቶች ወደ ሀገሪቱ እንዲያማትሩ እና አማራጮችን እንዲመለከቱ እያደረገ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ሁሉን አቀፍ ሪፎርም በማድረግ የጀመረችው ጉዞ በትክክለኛ የዕድገት ጎዳና ላይ እንድትቀመጥ ማስቻሉንም ጠቅሰዋል፡፡ በኢትዮጵያ በተጨባጭ ኢንቨስት እያደረጉ ያሉ የኦስትሪያ ኩባንያዎች መኖራቸውን ጠቅሰው ይህንን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚፈልጉ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የያዘችው ትክክለኛ የልማት ጎዳና ዓለም አቀፍ ባለሀብቶችን እየሳበ በመሆኑ ማሻሻያው ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል። የኢኮኖሚ ተሳትፎ፣ የትምህርት ትብብር እና የባህል ልውውጥን ጨምሮ የሁለቱ ሀገራት ሁለንተናዊ ግንኙነት ይበልጥ እንደሚጠናከርም ጠቁመዋል፡፡
ከተሞችን ለኢንቨስትመንት፣ ንግድና ቱሪዝም የተመቹ የማድረግ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jul 21, 2026 93
ከሚሴ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፦በኢትዮጵያ ከተሞችን ለኢንቨስትመንት፣ ንግድና ቱሪዝም የተመቹ የማድረግ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የከተማና መሰረት ልማት ሚኒስትር ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ ገለጹ። የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት በከሚሴ ከተማ "የኢትዮጵያ ከተሞች የኮሪደር ልማት" በሚል መሪ ሃሳብ ያዘጋጀው ስለ ኢትዮጵያ የተሰኘ የምክክር መድረክ እየተካሄደ ነው።   ሚኒስትሯ ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፣ የከተሞችን ፈጣን እድገት በማስቀጠል ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ ነው። የከተሞችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት ለማፋጠን በመሰረተ ልማት ግንባታ፣ ፈጣንና ተጠያቂነት ያለው አገልግሎት በመስጠት ላይ ተመስርቶ እየተካሔደ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በተለይ በኮሪደር ልማት፣ በመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት፣ በዲጂታላይዜሽንና የስማርት ሲቲ ትግበራ ከተሞችን ለኢንቨስትመንት፣ ለቱሪዝምና ንግድ ተመራጭ የማድረግ ስራ ትኩረት የተሰጠው ነው ብለዋል። ይህም ለወጣቶች የስራ እድል በመፍጠር፣ በእውቀት ሽግግርና ልምድ በመቅሰም ኢትዮጵያ በአስተማማኝ የእድገት መሰረት ላይ እንድትጓዝ የሚያስችል መሆኑን አስገንዝበዋል። በከተሞች በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ ዜጎችን ታሳቢ ባደረገ መልኩ የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለልም በመንግስት፣ በማህበርና በባለሃብቶች የተጀመረው የቤት ግንባታ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ይህም ከፍተኛ መነቃቃትና ተስፋ ከመፍጠሩ ባለፈ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚያግዝ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ በቅንጅት መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል። በአማራ ክልል የኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አህመድ አሊ በበኩላቸው፣ በዞኑ የሚገኙ ከተሞችን በኮሪደር ልማትና በሌሎችም መሰረት ልማቶች ተጠቃሚ የማድረግ ስራ እየተከናወነ ነው ብለዋል።   ይህም አመራሩ ከህብረተሰቡ ጋር ያለውን ቅንጅታዊ አሰራሮችን እንዲያጠናክር ከማድረጉም በላይ የዞኑን ሰላም በመጠበቅ በኩል ለውጥ ማስገኘቱን አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት የጀመራቸው መድረኮች ከተሞችን ከማነቃቃት ባለፈ በሀገር ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና አንድነት ላይ መወያየት እንዲቻል ምቹ ሁኔታ የፈጠረ መሆኑንም ገልጸዋል። በምክክሩ የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና የከተማ አመራሮች፣ አባ ገዳዎች፣ የሐይማኖት አባቶች፣ የሐገር ሽማግሌዎችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።
በደቡብ ወሎ ዞን በበልግ ወቅት ከለማው መሬት ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቧል
Jul 21, 2026 80
ደሴ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፦በደቡብ ወሎ ዞን በበልግ ወቅት የእርሻ ስራ ከለማው መሬት ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ይመር ሰይድ ለኢዜአ እንደገለፁት፣ በዞኑ በመኸር፣ በመስኖና በልግ ሰብል ልማት አርሶ አደሩን በንቃት በማሳተፍ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ ጥረት እየተደረገ ነው። በዚሁ ወቅት ከ104 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ቦሎቄ ፣ ማሾ ፣ ጤፍ ፣ ስንዴ ፣ ሽምብራና ምስር ሰብሎችን ማልማት መቻሉን ገልጸዋል። ምርታማነቱን ለማሳደግም ግብአትን በአግባቡ በመጠቀምና ተገቢውን እንክብካቤ በማድረግ ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። በበልግ ሰብል ልማት ከተገኘው ምርት በተጨማሪ ተረፈ ምርቱን ለእንስሳት መኖነት በመጠቀም የወተትና የስጋ ምርትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እንዲጨምር አስችሏል ብለዋል። የበልግ ዝናቡ ለሰብል ልማት ምቹ እንደነበር አውስተው አሁን ላይ ሰብሉን ቀድሞ በማንሳት ለመኸር ሰብል ልማት ዝግጁ የማድረግ ስራ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። በዞኑ አርጎባ ብሄረሰብ ልዩ ወረዳ የ07 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር የሱፍ አህመድ እንዳሉት፣ በዘንድሮው የበልግ ዝናብ ከአንድ ሄክታር መሬት በላይ ማሾና ቦሎቄ ማልማት ችለዋል። ካለሙት መሬት ላይም 12 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን ጠቁመው ከፍጆታ የተረፈውን በመሸጥ ጥሪት ለማፍራት ማቀዳቸውን ተናግረዋል። ሌላው የተሁለደሬ ወረዳ 013 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ኢብራሂም ደምስ በበኩላቸው፣ በበልግ ዝናብ ካለሙት አንድ ሄክታር መሬት የተሻለ ምርት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ከእለት ፍጆታ የተረፈውን ምርትም ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል ።
በምስራቅ ጎጃም ዞን የሰው ሰራሽና ተፈጥሮ አደጋን በራስ አቅም ለመቋቋም ርብርብ እየተደረገ ነው
Jul 21, 2026 73
ደብረ ማርቆስ ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፦በምስራቅ ጎጃም ዞን ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመቋቋምና በምግብ ራስን ለመቻል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የዞኑ አደጋ መከላከልና ስራ አመራር ተጠሪ ጽህፈት ቤት ገለጸ። የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ተሾመ መኮነን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በምግብ ራስን ለመቻል መንግስት ያስቀመጠውን አቅጣጫ ተግባራዊ በማድረግ በኩል ሁሉን አቀፍ ጥረት እየተደረገ ይገኛል። በተለይም በአካባቢው ዝናብ አጠር ፣ ጎርፍና በረዷማ በሆኑ ወረዳዎች ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች ሲገጥም በራስ አቅም ምላሽ ለመስጠት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ለዚህም በተያዘው የክረምት ወቅት ከሁለት ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት የሚያጋጥሙ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ ችግሮችን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በሁሉም ወረዳዎች ከ400 ሄክታር በላይ መሬት ደጋግሞ የታረሰ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 40 ሄክታር የሚሆነውን በስንዴና በጤፍ ዘር መሸፈኑን ገልጸዋል። ከዚህም ከ96 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም ነው ያስረዱት። ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግም ከሰባት ሺህ 500 ኩንታል በላይ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በማሰራጨት አርሶ አደሩ ጥቅም ላይ እንዲያውለው መደረጉን አብራርተዋል። የደጀን ወረዳ የየትኑራ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መኩሪያው ፈለቀ፤ ከተረጅነት ለመላቀቅ በሚደረገው ጥረት ውስጥ የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን አስረድተዋል። በቀበሌያቸውም በምግብ ራስን ለመቻል የሚያጋጥሙ ክፍተቶችን ለመሙላት በሚደረገው ጥረት ውስጥ በመሳተፍ ለዚሁ የተዘጋጀውን መሬት የማረስ ስራ ላይ እየተሳተፉ መሆኑን ገልፀዋል። የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ነገሰ ኑሬ በበኩላቸው ፤በቡድን በመሆን በምግብ ራስን ለመቻል የተለየውን መሬት በማረስ ለዘር ዝግጁ አድርገው እየተጠባበቁ መሆኑን ገልፀዋል ። ማሳውን በዘር ከመሸፈን ባለፈ በአረም፣ ሰብሉን ከተባይ በመከላከልና ከመንከባከብ ጀምሮ እስከ ሰብል ስብሰባው ድረስ በመሳተፍ ድርሻቸውን እንደሚወጡ አስረድተዋል። በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በምግብ ራስን ለመቻል በተደረገው እንቅስቃሴ ከ104 ሚሊዮን ብር በላይ ከማህበረሰቡ በማሰባሰብ ጥቅም ላይ ማዋል መቻሉን ከተጠሪ ጽህፈት ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ኢትዮጵያ በልማት እንቅስቃሴዎችና በውጭ ግንኙነት መስክ ተጨባጭ ውጤቶችን እያስመዘገበች ትገኛለች
Jul 20, 2026 740
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በልማት እንቅስቃሴዎችና በውጭ ግንኙነት መስክ ያስመዘገበቻቸው ውጤቶች የሀገሪቱን ሁለተናዊ ብልፅግና ከማረጋገጥ ባለፈ የውሳኔ ሉዓላዊነትን በተግባር ያረጋገጡ መሆናቸውን ምሁራን ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማሲና ዓለምአቀፍ ግንኙነት መምህር እንዳለ ንጉሤ እንደገለጹት፤ በፖለቲካ ሳይንስና ዲፕሎማሲ መስክ ሉዓላዊነት ሀገራት በውስጣዊም ሆነ በውጭ ጉዳዮቻቸው ላይ ያለማንም ጣልቃ ገብነት በነፃነት የመወሰን ሙሉ ባለቤትነትን ማረጋገጥ መቻል ነው። ከለውጡ በኋላ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟን ማዕከል ያደረገ የዲፕሎማሲ አካሄድ እየተከተለች እንደምትገኝ ገልፀው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅና ወደ ሥራ ማስገባት የመወሰን ነጻነት የታየበት ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ሕጋዊና ሞራላዊ መሠረት ያለው የባህር በር የማግኘት ጥያቄን በማንሳት ለዓለም ማህበረሰብ የማስገንዘብ ተግባር እያከናወነች መሆኗም የውሳኔ ሉዓላዊነቷ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። በሀገር ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያን ሁለተናዊ ዕድገት ከማረጋገጥ ባለፈ፣ ለአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች መጠናከር ያላቸውን ቁልፍ ሚና በግልጽ ያሳያሉ ብለዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ዶክተር መብራቱ አለሙ በበኩላቸው የዲፕሎማሲ አቅም ከሀገር ውስጥ የኢኮኖሚ ጥንካሬ ጋር የተሳሰረ መሆኑን ገልፀዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት መንግስት ወደ ተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ትግበራ መግባቱ የውጭ ምንዛሬ እጥረት፣ የዕዳ ጫናና የዋጋ ንረት ችግሮችን መፍታት ማስቻሉን አንስተዋል። የግል ዘርፉን በማጠናከር፣ የውጭ ባንኮችና ካፒታል ወደ ሀገር እንዲገቡ በር በመክፈትና የካፒታል ገበያን ስርዓትን በመዘርጋት የሀገሪቱን የፋይናንስ አቅም ማሳደጉን ገልፀዋል። በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚም የኤክስፖርት መጠንን በማሳደግና በብድርና በእርዳታ ላይ ያለውን ጥገኝነት በመቀነስ የውሳኔ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በከተሞች በኮሪደር ልማት እየተመዘገበ ያለው ፈጣን እድገት የሀገሪቱን ዓለምአቀፍ ገጽታና የኮንፍረንስ ቱሪዝም ማዕከልነት እያሳደገ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟን ማዕከል ያደረገ ባለብዙ ዘርፍ ዲፕሎማሲና ለጎረቤት ሀገራት ቅድሚያ የመስጠት መርህን እየተከተለች መሆኗም ለዲፕሎማሲ ስኬቷ መሰረት መሆኑን ምሁራኑ ተናግረዋል።
በኦሮሚያ ክልል በተካሄደ የኦዲት ክትትል ግኝቶች ላይ አስፈላጊው የማስተካከያ እርምጃ እንዲወሰድ ተደርጓል 
Jul 20, 2026 636
አዳማ፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በተካሄደ የኦዲት ክትትል ግኝቶች ላይ አስፈላጊው የማስተካከያ እርምጃ እንዲወሰድ መደረጉን የክልሉ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ኃላፊ አቶ ተፈሪ ወንድይፍራው ተናገሩ። ለሁለት ቀናት የተካሄደው የጨፌ ኦሮሚያ 6ኛ የሥራ ዘመን 5ኛ ዓመት 11ኛ መደበኛ ጉባዔ የክልሉን ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ሪፖርትን እና የዳኞች ሹመትን በማፅደቅ ተጠናቋል።   የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የክልሉ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤትን ሪፖርት ያቀረቡት ኃላፊው አቶ ተፈሪ ወንድይፍራው፤ የመንግሥት ገቢ እና ወጪ በሕግና መመሪያ መሠረት መሰብሰቡን እና መውጣቱን ለማረጋገጥ ኦዲት መደረጉን ተናግረዋል። በኦዲት ሥራውም በ48 መሥሪያ ቤቶች 195 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ሳይሰበሰብ መገኘቱን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ከ220 ሚሊዮን ብር በላይ ሕግን ሳይጠብቅ የበጀት ዝውውር ሥራ ላይ መዋሉ በተደረገው ኦዲት መገኘቱንም ገልጸዋል። በተከናወነው የኦዲት አፈጻጸም ክትትል በታዩት ግኝቶች ላይ አስፈላጊው የማስተካከያ እርምጃ መወሰዱን ጠቅሰዋል። በ16 መሥሪያ ቤቶች ላይ በተደረገ ክትትልም በኦዲት ሪፖርቱ በተሰጠው የማሻሻያ ሐሳብ መሠረት የተለያዩ እርምጃዎች መወሰዳቸውን ጠቁመዋል። በ2019 በጀት ዓመትም ለብልሹ አሠራር ተጋላጭ በሆኑ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችና የልማት ድርጅቶች ውስጥ ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ የኦዲት አገልግሎት ይጠናከራል ብለዋል። በክልሉ የበጀት፣ የንብረትና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ በእጥፍ እየጨመረ በመሆኑ የመሥሪያ ቤቱ ባለሙያዎችን አቅምና ብቃት ማሳደግ፣ የንብረት ክትትልና ቁጥጥርን ማጠናከር እንዲሁም የኦዲት ሽፋንን ማሳደግ ላይ በትኩረት እንደሚሠራ ገልጸዋል። በኦሮሚያ ጨፌ የመንግሥት በጀትና የሀብት ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴም የዋናው ኦዲተር መሥሪያ ቤት የተሰጠውን ኃላፊነት በአግባቡ ለመወጣት የተለያዩ የኦዲት ዓይነቶችን ሲያካሂድ መቆየቱን ገልጿል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ገመቹ አራርሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤ የመንግሥት አሠራር ባልተከበረባቸው ቦታዎች ላይ በኦዲት ግኝቶች ላይ የተመሠረተ እርምጃ እንዲወሰድ ሲደረግ መቆየቱን ተናግረዋል።
በደብረ ብርሃን ከተማ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠቃሚ አድርገውናል
Jul 20, 2026 678
ደብረብርሃን፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦ በደብረ ብርሃን ከተማ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ዘላቂ ተጠቃሚነታችንን ያረጋገጡ ናቸው ሲሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። ከደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ በለጡ አስፋው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተማዋ የልማት፣ የሰላምና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች በትኩረት መሰራታቸው ተጠቃሚ እንድንሆን አድርጎናል ብለዋል። በተለይም ወንጀል ይፈፀምባቸው የነበሩ አካባቢዎችን በማልማት ውብ፣ ሳቢና ማራኪ የመዝናኛ ስፍራ እንዲሆን መደረጉ በተሻለ መንገድ ነዋሪውን ተጠቃሚ ለማድረግ ያስቻሉ ናቸው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የከተማዋን አድገት በሚያፋጥኑ የልማት ስራዎች ላይ በጉልበት፣ በገንዘባቸው እና በእውቀታቸው በመሳተፍ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ገልጸዋል። ሌላው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ሠይድ ማሩ በበኩላቸው፤ በከተማው የተካሄዱ የመንገድና ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ለወጣቶችና ለሴቶች የሥራ ዕድልን የፈጠሩ ናቸው ብለዋል። የተገነቡ የመሰረተ ልማቶች የአገልግሎት ጊዜያቸው እንዲረዝም የአካባቢውን ማህበረሰብ በማስተባበር የመጠበቅና የመንከባከብ ስራ እየሰሩ መሆኑን ነው ያመለከቱት። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሽት በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተከናወኑ የልማት ስራዎች ከተማዋን የኢንዱስትሪ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ማእከል እንድትሆን ያስቻሉ ናቸው።   በዚሁ ወቅት ሰላምን ከማስጠበቅ ጎን ለጎን ህብረተሰቡ የተሳተፈበት የ75 ኪሎ ሜትር የጠጠርና ሶስት ኪሎ ሜትር የኮብል ስቶን መንገዶች መገንባታቸውን አስረድተዋል። በተለይም በከተማዋ የተገነባው የሶስት ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ ደረጃውን የጠበቀ የእግረኛና የሳይክል መንገዶችን ጨምሮ የመዝናኛ እና የአረንጓዴ ስፍራዎችን ያካተተ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የቴሌኮሙኒኬሽንና የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማቶችን አሟልቶ የተገነባ በመሆኑ ለከተማዋ እድገትና ለህዝቡ ተጠቃሚነት የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ19 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ እድል መፈጠሩን ጠቁመው በአዲሱ በጀት ዓመትም ከዚህ የላቀ ስራ ለመስራት በቁርጠኝነት እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙ አመልክተዋል።
በአማራ ክልል በ42 የተለያዩ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ ተከናውኗል
Jul 20, 2026 110
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ) ፡-በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ42 የተለያዩ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ መከናወኑን የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ አስታወቀ። የአማራ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ አማካሪ ሽቤ ክንዴ፤ በተለይም በከተሞች ልማት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተከናወኑ አበይት ተግባራትን በተመለከተ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም በክልሉ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራዎችን በማስፋፋት ዘመናዊ በማድረግ ለኑሮ፣ ለኢንቨስትመንትና ለጉብኝት ጭምር ምቹ ማድረግ ስለመቻሉ አንስተዋል። በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ42 የተለያዩ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ ስለመከናወኑ ጠቅሰው በዚህም የዜጎችን ተጠቃሚነት እውን ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የኮሪደር ልማቱ የእግረኛ፣ የተሽከርካሪ፣ የብስክሌት መንገድን ጨምሮ የአረንጓዴ ልማት፣ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች፣ የመዝናኛ ስፍራዎችና መሰል አገልግሎቶችን አካቶ የተሰራ መሆኑን ጠቅሰው በተያዘው በጀት ዓመትም ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በልማቱ ከ214 ኪሎ ሜትር በላይ የመንገድ ስራ እንዲሁም ከ100 ሄክታር በላይ የተለያዩ አካባቢዎችን በአረንጓዴ ልማት የማስዋብ ስራ ተሰርቷል ብለዋል። በዚህ የልማት ስራ ከ199 ሺህ 700 ለሚበልጡ ወገኖች የስራ እድል ስለመፈጠሩ አንስተው ልማቱ ቀጣይነት ይኖረዋል ብለዋል። የአንድ ከተማ አንድ ፕሮጀክት የልማት እንቅስቃሴም በ205 ከተሞችና ክፍለ ከተሞች 281 ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ሲሆን አብዛኞቹ ተጠናቀው ለህዝብ አገልግሎት እንዲውሉ መደረጉንም አንስተዋል። በቀጣይም ልማቱን ወደ ሌሎች ከተሞች ለማስፋት መታቀዱን ያነሱት አቶ ሽቤ፤ የዜጎች እገዛና ተሳትፎ ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
የገበያ አማራጮችን በማስፋትና ህገ ወጥነትን በመቆጣጠር ለገበያ መረጋጋት የሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jul 20, 2026 74
ኮምቦልቻ ፤ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፡- የገበያ አማራጮችን በማስፋት፣ የምርት አቅርቦትን በማሳለጥና ህገ ወጥነትን በመቆጣጠር ለገበያ መረጋጋት የሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን የአማራ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የተጠናቀቀው በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ግምገማና የአዲሱን በጀት ዓመት እቅድ የትውውቅ መድረክ በኮምቦልቻ ከተማ እያካሄደ ነው።   በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የአማራ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢብራሂም መሐመድ (ዶ/ር)፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በገበያ አቅርቦትና ዋጋን በማረጋጋት ረገድ ብዙ ስኬታማ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም የገበያ አማራጮችን በማስፋት፣ የምርት አቅርቦትን በማሳለጥና ህገ ወጥነትን በመቆጣጠር ለገበያ መረጋጋት የሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።   የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ንግድንና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ዮናስ መላኩ፤ በከተማው የገበያ ማዕከላትን በማስፋፋት የምርት አቅርቦትና ተደራሽነት ላይ በቅንጅት መሰራቱን አንስተው ቀጣይነት የሚኖረው መሆኑን አረጋግጠዋል። በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የወረዳዎች በየደረጃው ያሉ የስራ ሃላፊዎችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው።  
ብልጽግና ፓርቲ በተለያዩ ኢኒሼቲቮች በርካታ ስኬቶችን አስመዝግቧል-አቶ አደም ፋራህ
Jul 20, 2026 676
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ባለፉት ዓመታት የብልጽግና ፓርቲ የተለያዩ ኢኒሼቲቮችን በመቅረጽ ወደ ተግባር በማስገባት በርካታ ስኬቶችን ማስመዝገቡን የፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ ገለጹ። በአቶ አደም ፋራህ የተመራ የፓርቲው የዋናው ጽህፈት ቤት እና የክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት አመራሮች ቡድን በአዲስ አበባ ከተማ እየተከናወነ ያለውን የተቋማት ግንባታ ስራ ተዘዋውሮ ተመልክቷል። አቶ አደም ፋራህ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በብልጽግና ፓርቲ መሪነት የተከናወኑ የተለያዩ ስራዎች ስኬት አስመዝግበዋል።   የተለያዩ ኢኒሼቲቮችን በመቅረጽ ዘርፈ ብዙ ስራዎች ተከናውነው በርካታ ስኬት መምጣቱን አንስተው፤ የተመዘገበውን ስኬት ይበልጥ አጠናክሮ ማስቀጠል የፓርቲው ቀጣይ ትኩረት መሆኑንም አብራርተዋል። አመራሮቹ ከጉብኝት ባለፈ በመዲናዋ ባሉ የፓርቲው ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች ችግኝ በመትከል አረንጓዴ ዐሻራቸውን አኑረዋል።
በጌዴኦ ዞን ከ44 ሺህ 700 ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ወደ ተግባር ተገብቷል
Jul 20, 2026 98
ዲላ፤ ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን በ2018/19 የመኸር አዝመራ ወቅት ከ44 ሺህ 700 ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ትግበራ መገባቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለጸ። በመኸር አዝመራው ከሚለማው መሬት ከ7 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱም ተመልክቷል።   በዞኑ የመኸር አዝመራ ንቅናቄ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ በመኸር እርሻ ወቅት ሊለማ የሚችልን መሬት ወደ ልማት በማስገባት የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ ይሠራል ብለዋል። በተለይም መሬትን ደጋግሞ በማረስና የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሻሻል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት ተሠርቷል ነው ያሉት። ዞኑ ከቡናና ከሌሎች ቋሚ ሰብሎች ጎን ለጎን በተያዘው መኸር ፈጥነው የሚደርሱና የምግብ ዋስትና ክፍተትን የሚሸፍኑ ሰብሎችም እንደሚለሙ ገልጸዋል። ለዚህም ምርጥ ዘርና ማዳበሪያን ጨምሮ የግብዓት ስርጭት በወቅቱ እንዲከናወን ከማድረግ ባለፈ አርሶ አደሩ በኩታ ገጠም እንዲያለማም የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል። የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ተገኝ ታደሰ በበኩላቸው፣ በመኸር አዝመራው 44 ሺህ 715 ሄክታር መሬት በሰብል ለማልማት ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል።   ከዚህ ውስጥም 26 ሺህ 158 ሄክታር መሬት በአዝዕርት፣ አትክልትና ስራስር ሰብሎች የሚለማ ሲሆን በተለይ ገብስ፣ ጤፍ፣ ስንዴ፣ አተር፣ ባቄላና ድንች ዋና ዋናዎቹ ናቸው ብለዋል። የተቀረው በእንሰትና ፍራፍሬ የሚሸፈን መሆኑን አንስተው በአጠቃላይ ከተያዘው የመኸር አዝመራ ከ7 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱን ተናግረዋል። እቅዱን ለማሳካት የማሳ ዝግጅትና የግብዓት ስርጭት መከናወኑን አንስተው በየደረጃው የሚገኝ የግብርና አመራርና ባለሙያ በቅንጅት እየሠሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በንቅናቄ መድረኩ የዞንና የሁሉም ወረዳዎች አስተዳዳሪዎች፣ የዘርፉ የሥራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።  
በድሬደዋ ከ71 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወሰዱ
Jul 20, 2026 127
ድሬደዋ፣ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦በድሬደዋ አስተዳደር በበጀት አመቱ ከ71 ቢሊዮን ብር በላይ ያስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መውሰዳቸውን የአስተዳደሩ ኢንቨስትመንት ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የኢንቨስትመንት ፕሮጀክት ጥናት፣ መረጃ ዝግጅትና ፕሮሞሽን ቡድን አስተባባሪ አቶ አበራ መንግስቱ ዛሬ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት በቀየሰው ምቹ ሁኔታ በበጀት አመቱ ከ71 ቢሊዮን 304 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ 464 ባለሃብቶች ፈቃድ ወስደዋል። በአምራች ኢንዱስትሪ፣በአገልግሎት፣በኮንስትራክሽንና በግብርና ዘርፎች ፈቃድ የወሰዱት አልሚዎችም ሙሉ በሙሉ ወደ ስራ ሲገቡ ከ21 ሺህ 650 በላይ ቋሚና ጊዜያዊ የስራ ዕድል ይፈጥራሉ ብለዋል። አስተዳደሩ አልሚዎቹን ውጤታማ ለማድረግ መሠረተ ልማቶችን ከማሟላት ባሻገር ክትትልና ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በአስተዳደሩ የተተገበረው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ፣የተቀናጀ ድጋፍ እና ክትትል የኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት በማሳደግ ተኪ ምርቶችን ማሳደግና የውጭ ምንዛሬን ማስፋት መቻሉን ጠቅሰዋል።   በዚህም በርካታ ኢንዱስትሪዎችም ከመካከለኛ ወደ ከፍተኛ ደረጃ ማደግ እንደቻሉና ለዜጎችም የስራ ዕድል እንዲፈጥሩ ማገዙን ገልጸዋል። ይህም ድሬደዋን በኢንቨስትመንት ዘርፍ የምስራቅ ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ማዕከልነቷን ከማሳደግ በላይ የአስተዳደሩን ማህበራዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ እንቅስቃሴዎች በከፍተኛ ደረጃ ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። በኢንቨስትመንት ዘርፉ ፈቃድ ወስደው እንቅስቃሴ ለጀመሩ ባለሃብቶች ከአስተዳደሩ መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ጋር በመቀናጀት ከ50 ሄክታር መሬት በላይ መቅረቡን አቶ አበራ ጠቁመዋል። ኢንቨስትመንቱን ለማስፋትም የመስሪያ ማሽኖችን ከታክስ ነፃ እንዲያስገቡ መደረጉንና የፋይናንስ፣የውሃ፣ የመንገድና የኤሌክትሪክ አገልግሎቶች እንዲሟሉ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በትብብር መሰራቱን አንስተዋል። በሆቴልና በቡና ማቀናበር ዘርፍ ፍቃድ ከወሰዱ ባለሃብቶች መካከል አቶ ተካልኝ አበበ እና አቶ አብዱልጀባር አሊ በበኩላቸው፥ አስተዳደሩ ለባለሃብቶች እየፈጠረ የሚገኘው ምቹ የስራ አካባቢና የሚያደርገው ድጋፍ አስደሳች መሆኑን ገልጸዋል።  
የሕዳሴ ግድብ የዘመናት ኢ-ፍትሐዊነትን የሻረ የጋራ ተጠቃሚነት ተምሳሌት ነው
Jul 20, 2026 695
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በዓባይ ወንዝ ላይ ነበረውን የዘመናት ኢ-ፍትሐዊ የውሃ ሃብት አጠቃቀም ያስወገደ፣ አዲስ የትብብር እና የጋራ ተጠቃሚነት ተምሳሌት መሆኑን የሕዝብ ተወካች ምክር ቤት አባል መሐመድ አል-አሩሲ ገለጹ፡፡ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን የታሪክ ቁጭታቸውን በተግባር ለመቀየር የቆረጡበትና በማንኛውም ውጫዊ አካል ሳይሆን በራሳቸው የውስጥ አቅምና በሕዝብ ሁለንተናዊ አስተዋጽኦ ብቻ የተገነባ ታሪካዊ ፕሮጀክት ነው። ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት አገሪቱ ካላት የተፈጥሮ ሀብት ተጠቃሚ ለመሆን የምታደርገውን ጥረት የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ፣ በታዳሽ ኃይል ልማት ረገድ የኢኮኖሚና የቴክኖሎጂ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የጀመረችውን ስልታዊ ጉዞ በግልጽ ያሳያል። ይህ የኢትዮጵያውያን የመቻል አቅም ማረጋገጫ የሆነው ሜጋ ፕሮጀክት፣ የአፍሪካ አገራት የራሳቸውን የውስጥ አቅም አስተባብረው ከተንቀሳቀሱ ያለምንም ውጭ ድጋፍ ትልልቅ የልማት ግቦችን ማሳካት እንደሚችሉ ትልቅ ማሳያ ሆኗል። በመሆኑም ግድቡ ለአፍሪካ አህጉር ነፃነትና ራስን የመቻል አዲስ ተስፋን በማስረፅ ረገድ ታላቅ ኩራትና የማይደበዝዝ የታሪክ ትምህርት የሰጠ ሆኖ ተመዝግቧል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል መሐመድ አል-አሩሲ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ግብፅ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ የምታነሳቸው ነጥቦች ታሪካዊ እውነታዎችን፣ የላይኛው ተፋሰስ አገራትን የልማት መብት እንዲሁም ዓለም አቀፍ የውሃ አስተዳደር ሕጎችን የሚጋፉ መሆናቸውን አስረድተዋል። ይህ የግብፅ አካሄድ ጊዜ ያለፈበትን የውሃ የበላይነት ዘመን እንደገና ለማንፀባረቅ የሚደረግ ዋጋ ቢስ ሙከራ መሆኑንም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው ተግባራት በሙሉ ዓለም አቀፋዊ መርሆዎችን የተከተሉ መሆናቸውን የምክር ቤት አባሉ አብራርተዋል። ዓለም አቀፍ ሕግ የላይኛው ተፋሰስ አገራትን ያገለለ እና በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈረሙ ስምምነቶችን እንደማይቀበል የገለጹት አቶ መሐመድ፣ ኢትዮጵያ፣ ግብፅ እና ሱዳን በ2015 ዓ.ም በካርቱም የፈረሙትን የመርሆች መግለጫ በማስታወስ ግድቡን የመሙላት ሂደት ከዚህ ስምምነት ጋር በሚጣጣም መልኩ መከናወኑን አስረድተዋል። ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ የገነባችው ታላቁ የህዳሴ ግድብ የቀደመውን ኢ-ፍትሃዊ አሰራር በመቀየር፣ መላውን የናይል ተፋሰስ ይበልጥ ፍትሃዊ፣ ምክንያታዊ እና ሁሉን አቀፍ በሆነ መንገድ ለመምራት የሚያስችል ታሪካዊ ሽግግር መፍጠሩንም ገልጸዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያውያን የውስጥ አቅምና ሀብት የተከናወነ መሆኑን ነው ያስታወሱት መሐመድ አል-አሩሲ፣ ፕሮጀክቱ የሕዝቡን የልማትና የእድገት ፍላጎት በግልጽ የሚያሳይ የታሪክ አሻራ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህም ኢትዮጵያ ግድብ መገንባት ብቻ ሳይሆን፣ በናይል ተፋሰስ ቀጠና ውስጥ አዲስ የፍትህ እና የእኩልነት ታሪክ ጽፋለች ብለዋል። ግብፅ የድርድር ሂደቱን በተደጋጋሚ በማዘግየትና ከግድቡ ቴክኒካዊ ወሰን ውጭ የሆኑ ሰፊ የውሃ ክፍፍል አጀንዳዎችን በማንሳት የፕሮጀክቱን ጉዞ ለማደናቀፍ ስትሞክር መቆየቷን የፓርላማ አባሉ አስታውሰዋል።
በድሬዳዋ ባለፉት ዓመታት የተመዘገቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስኬቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jul 19, 2026 269
ድሬዳዋ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ ባለፉት አምስት ዓመታት በልማትና በመልካም አስተዳደር የተመዘገቡ ስኬቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የመንግስት ዋና ተጠሪ ኢብራሒም ዩሱፍ ገለጹ። የአስተዳደሩ ምክርቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ኢብራሒም ዩሱፍ ዛሬ በሰጡት መግለጫ እንደገለጹት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። በተለይ የገጠርና የከተማ ነዋሪዎችን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በተቀናጀ መንገድ ለመፍታት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን አንስተዋል። የድሬዳዋን የንግድ፣ የኢንዱስትሪ እና የአገልግሎት ማዕከልነት በተጨባጭ ያረጋገጡ አዳዲስ አምራች ኢንዱስትሪዎች እንዲሁም ደረጃቸውን የጠበቁ ዘመናዊ ሆቴሎችና የሎጅስቲክ ማሳለጫ ማዕከላት ተገንብተው ለአገልግሎት መብቃታቸውን አስረድተዋል። በተለይ በመጀመሪያው ምዕራፍ በከተማዋ ዋና ዋና አካባቢዎች ከ16 ኪሎ ሜትር በላይ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ድሬዳዋን ጽዱ፣ ውብና ለኑሮ ተመራጭ እያደረጋት መምጣቱን ገልጸዋል። ታሪካዊ ቅርሶችን በጠበቀና ገጽታዋን በሚገነባ መልኩ የተከናወነው የኮሪደር ልማት በከተማዋ አዳዲስ መሠረተ ልማቶች እንዲስፋፉ ማድረጉንም ጠቁመዋል። መሰረተ ልማቶቹ ባለሀብቶችን ከመሳብ በተጨማሪ የትራፊክ መጨናነቅን በማስቀረት የተሽከርካሪ አደጋን ለመቀነስ አስችለዋል ብለዋል። በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የፌደራልና የአስተዳደሩ ተቋማት ተቀናጅተው ፈጣንና ቀልጣፋ ዲጂታል አገልግሎት በመስጠታቸው የዘመናት የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን እየፈታ መሆኑንም አቶ ኢብራሒም ተናግረዋል። እንደ እሳቸው ገለጻ በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን ለሕብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ የኑሮ ውድነትን ማቅለል የሚያስችል ውጤታማ ሥራ ተከናውኗል። በአስተዳደሩ አገልግሎት መስጠትና ማምረት በጀመሩ ተቋማትና ኢንዱስትሪዎች በብዙ ሺህ ለሚገመቱ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉንም የመንግስት ዋና ተጠሪው አንስተዋል። በኢንተርፕራይዝ የተደራጁ ወጣቶችን ውጤታማ ለማድረግ የስልጠና፣ የመስሪያ ቦታ፣ የብድርና የሙያ ድጋፍ መሰጠቱንም አመልክተዋል። ባለፉት 5 ዓመታት በሁሉም ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤቶችን በላቀ ደረጃ ለማሳደግ አስተዳደሩ የተቀናጀ እንቅስቃሴ መጀመሩንም አቶ ኢብራሒም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም