ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ውጤታማ ናቸው
Aug 23, 2026 170
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 17/2018 (ኢዜአ)፡- በባህር ዳር ከተማ አስተዳደር በቅንጅት የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ውጤት ማምጣታቸውን የከተማዋ ተቀዳሚ ምክተል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተከናወኑ የመንግስትና የፓርቲ ስራዎችን አፈጻጸም በመገምገም ላይ ይገኛል። በመድረኩ የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው እንደገለጹት፣ የከተማዋን ሰላምና ልማት ዘላቂ ለማድረግ በቅንጅት የተከናወኑ ተግባራት ውጤት አምጥተዋል። በፖለቲካው ዘርፍም የመደመር መንግስት እሳቤዎችን መሰረት በማድረግ፣ አሰባሳቢ ትርክት የመገንባትና አሳታፊ የፖለቲካ መስመሮች መዘርጋታቸውን ጠቁመዋል። ለአብነትም በ7ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ህዝቡን በነቂስ ወጥቶ ይበጀኛል ያለውን መንግስት በመምረጥ ሀገርን ማስቀደሙን አሳይቷል ብለዋል። ማህበራዊ ልማትን በማፋጠን ረገድም በትምህርት፣ በጤና እና የስራ አጥነት ችግርን በመፍታት ላይ ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውን አቶ ጎሹ አመላክተዋል። በከተማዋ ነዋሪዎች የቤት ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ለመስጠትም የቤት መስሪያ ቦታ መሰጠቱን አንስተዋል። የከተማዋን ገቢ ለማሳደግ የሚሰሩ የልማት ስራዎች፣ የቱሪዝም መዳረሻዎች እንዲሁም የኮሪደር እና የጣና ዳር ልማት ፕሮጀክቶች በተሳካ ሁኔታ መከናወናቸውን ገልጸዋል። በከተማዋ የተመዘገቡትን ልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን ለማስቀጠል ቅንጅታዊ ተግባራት በቀጣይም እንደሚጠናከር ገልጸዋል። በመድረኩ በየደረጃው ያሉ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
ከህዳሴ ግድብ እስከ ግዙፍ የአውሮፕላን ማረፊያ - የኢትዮጵያ አህጉራዊ የመሰረተ ልማት መሪነት
Aug 21, 2026 840
(በሙሴ መለሰ) መሰረተ ልማት የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ማዕዘን ከሆኑ ቁልፍ ዘርፎች መካከል የሚጠቀስ ነው። ኢትዮጵያ የነገ ብልጽግናዋን እውን ለማድረግና የዜጎቿን ፍትሀዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በተፋጠነ መልኩ እየተገበረቻቸው የሚገኙት ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ቁልፍ ሚና አላቸው ። በመንገድ፣ በባቡር፣ በኢንዱስትሪ ፓርኮች፣ የኮሪደር ልማት እና ሌሎች ግንባታዎች ላይ እያፈሰሰች ያለው መዋዕለ ንዋይ ኢትዮጵያን እና ህዝቦቿን የሚመጥን የኢኮኖሚ እድገት እና የአኗኗር ዘይቤን በመፍጠር ረገድ ያላቸው አስተዋጽኦም ቀላል አይደለም። ግዙፉ ፕሮጀክቶቿ መካከልም በጳጉሜን ወር 2017 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተመረቀው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለአፍሪካ የኢነርጂ ትስስር ውጥን ትልቅ የምስራች ሆኖ መጥቷል። የጎረቤት ሀገራት ከግድቡ የሚያገኙት የኤሌክትሪክ አቅርቦት ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከር ያስችላል። በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የተገኙ የሀገራት መሪዎች ባደረጉት ንግግርም በአጽንኦት ያረጋገጡት የህዳሴ ግድብ የአፍሪካ የራስን የመቻል ምልክት እና የኢትዮጵያን አይበገሬነት ተምሳሌትነት ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በህዳሴ ግድብ ምርቃት ወቅት የተለያዩ ግዙፍ መሰረተ ልማቶች ግንባታ እንደሚጀመር ይፋ አድርገዋል። የኒውክሌር ኃይል ማበልጸጊያ፣ የጋዝ ፋብሪካ ማስመረቅ፣ የነዳጅ ማጣሪያ እውን ማድረግ፣ በአፍሪካ ግዙፉ አየር ማረፊያ የሆነውን የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ መጀመር፣ ሁለተኛውን የጋዝ ፋብሪካ ግንባታ ማስጀመር፣ የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ ማስጀመር እና የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶች በመላው ሀገሪቱ ማስጀመር በጠቅላይ ሚኒስትሩ ይፋ የተደረጉ ፕሮጀክቶች/የጉባ ብስራቶች/ ናቸው። በሶማሌ ክልል የጋዝ ፋብሪካ የተመረቀ ሲሆን፣ በአፍሪካ ታሪክ በትልቅነቱ ቀዳሚ የሆነው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በግንባታ ሂደት ላይ ይገኛል። ይህ ግዙፍ የአየር ማረፊያ ፕሮጀክት የሀገሪቱን የሎጂስቲክስና የቱሪዝም አቅም ከመቀየር ባለፈ፣ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ያላትን የአቪዬሽን መሪነት ይበልጥ የሚያጠናክር ነው። ከዚህ ጋር ተያይዞ የሀገሪቱን የግብርና ምርታማነት በዘላቂነት ለመደገፍ ወሳኝ የሆነው የማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ እና የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶች ግንባታ በየክልሎቹ ካሉ የከተማ ማዘመንና የኮሪደር ልማት ስራዎች ጋር በተቀናጀ መልኩ ወደ ተግባር እየተሸጋገረ ይገኛል። በግንባታ ላይ የሚገኘው የኮይሻ የኤሌክትሪክ ኃይል ግንባታም ለኢነርጂ አቅርቦት እድገት የበኩሉን ሚና የሚጫወት ሲሆን፣ ሀገሪቱ የጀመረችውን የአረንጓዴ ኢነርጂና የኢንዱስትሪ ልማት ጉዞ በከፍተኛ ደረጃ ያፋጥነዋል። እነዚህ ግዙፍ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ሀገሪቱ በቅርቡ ከጀመረችው አጠቃላይ የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የገበያ መር ሥርዓት ጋር የተቆራኙ ስትራቴጂካዊ እርምጃዎች ተደርገው ይወሰዳሉ። የሀገር ውስጥ ምርታማነትንና የዜጎችን የኑሮ ጥራት ከመሰረቱ የሚያሻሽሉ ከመሆናቸውም በላይ፣ ሀገሪቱ በውጭ ዕርዳታና ብድር ላይ ከመደገፍ ወጥታ በሀገር ውስጥ እቅድና አቅም ላይ ተመስርታ የራሷን ዕድል የምትወስን አይበገሬነቷን በተግባር ያሳዩ የኩራት መገለጫዎች ናቸው። መንግሥት በነዳጅ፣ በጋዝ፣ በማዳበሪያ እና በ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቤቶች ግንባታ ላይ የጀመራቸው ግዙፍ ፕሮጀክቶች ቀደም ሲል የነበረውን የመንግሥትን ብቻ ፋይናንስ ጥገኝነት በመቀነስ፣ የሀገር ውስጥ እና የውጭ የግል ባለሀብቶችን (Private Sector) በከፍተኛ ደረጃ የሚያሳትፉ አዳዲስ የአጋርነት ሞዴሎችን የፈጠሩ ናቸው። የተቀናጁ መሰረተ ልማቶች ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያለውን የንግድና የኢኮኖሚ ትስስር በማላቅ ቀጣናዊ ትብብርን ወደ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ የሚያሸጋግሩ በመሆናቸው፣ ኢትዮጵያ በአህጉራዊ ትስስርና በአፍሪካ የነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነቶች ውስጥ ያላትን ተወዳዳሪነትና ተጠቃሚነት በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያሳድጉት አያጠራጥርም። በመሆኑም እነዚህን ስትራቴጂካዊ የካፒታል ፕሮጀክቶች ከተጀመሩት የከተማ ማዘመንና የኮሪደር ልማት ስራዎች ጋር መተሳሰር፣ ኢትዮጵያን የአፍሪካ የብልፅግና ተምሳሌትና የኢኮኖሚ ማዕከል አድርጎ ለመገንባት ለተቀመጠው የረጅም ጊዜ ሀገራዊ ራዕይ መሳካት አስተማማኝ ዋስትና ተደርገው ይወሰዳሉ። የመደመር መንግሥት የኢትዮጵያዊያንን የእድገት መሻት ለማሳካት የሚያከናውነው የተቀናጀ ስራ ተጠናክሮ የሚቀጥል ነው። ለዚህ ስኬት ደግሞ ሁሉም ዜጋ እጅ ለእጅ ተያይዞ በጋራ መንቀሳቀስ ይኖርበታል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመደመር መንግሥት መጽሐፋቸው ገጽ 221 ላይ እንዳመለከቱት አይበገሬነት አንድ አካል ለብቻው የሚወጣው ጉዳይ አይደለም ። ከብዙዎች ጋር ተደምረን የጋራ ጉዳይ መሆኑን ተግባብተን በመደጋገፍና በመተባበር የምንወጣው ጉዳይ ነው።
የኢትዮ-ቻይና ስትራቴጂካዊ አጋርነት ለቻይና-አፍሪካ ትብብር ትልቅ ተምሳሌት ነው - አምባሳደር ቼን ሃይ
Aug 21, 2026 482
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያና ቻይና በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂካዊ አጋርነት፣ በቻይና እና አፍሪካ መካከል የጋራ ተጠቃሚነትን ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ውስጥ ትልቅ አስተዋጽኦ እያደረገ እንደሚገኝ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ ገለጹ። ሁለንተናዊ ስትራቴጂካዊ ግንኙነቱ ቻይና እና ኢትዮጵያ በሁሉም አጋጣሚዎች አብረው የሚቆሙበትና በጋራ የሚሰሩበት ማዕቀፍ መሆኑን አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ወደ ሁለንተናዊ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ከፍ ማለቱ፣ የዓለም አቀፍ ትብብርንና የጋራ ዕድገት አቅም የሚያንጸባርቅ ከመሆኑም በላይ ለቻይና እና አፍሪካ ግንኙነት መጠናከር እንደ ዋና መሠረት እንደሚያገለግልም ተናግረዋል። ግንኙነቱ ከተለመደው የዲፕሎማሲ ወሰን በመሻገር፣ በጽኑ ፖለቲካዊ እምነትና በጠንካራ ወዳጅነት ላይ ወደተመሰረተ ሁለገብ አጋርነት ማደጉን አመልክተዋል። በሁለቱ ሀገራት መሪዎች ጥበበኛ አመራር የሁለትዮሽ አጋርነቱ በበርካታ ዘርፎች ጉልህ ውጤት እየተመዘገበበት መምጣቱንም ነው የገለጹት። በቅርብ ዓመታት በሁለቱ ሀገራት መሪዎች መመሪያ አማካኝነት ቻይና እና ኢትዮጵያ በፖለቲካውና በኢኮኖሚ ዘርፍ በጋራ እየሰሩ ነው ብለዋል። የሁለቱን ሀገራት ሕዝቦች ተጠቃሚነት ለማረጋገጥም ይበልጥ ትብብራቸውን እያጠናከሩ መሆኑን አንስተዋል። ሁለቱ ሀገራት የደቡብ ንፍቀ ዓለም (Global South) ድምፅ መሆናቸውን ገልጸው በብሪክስ (BRICS) ማዕቀፍ ውስጥ የነቃ ተሳትፎ እያደረጉ እንደሚገኝም አመልክተዋል። በነዚህ መድረኮች አማካኝነት ቻይና እና ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ የጠበቀ ትብብር እንዳላቸው ጠቅሰው፤ ፍትሃዊ የዓለም ስርዓት እንዲሰፍንም በጋራ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። ይህ አጋርነት በረጅም ዘመን ታሪካዊ ወዳጅነት ላይ የተገነባ መሆኑን የጠቀሱት አምባሳደሩ፤ አሁን ላይ የዘመኑን ጥያቄዎች በሚመልስ ፈጣን የእድገት ምዕራፍ ውስጥ እንደሚገኝ አብራርተዋል። በአዲሱ ዘመን ሁለንተናዊ ስትራቴጂካዊ አጋርነቱ በከፍተኛ ፍጥነት እንደሚያድግና በጋራ እጣ ፈንታ ላይ የተመሰረተ የቻይና እና አፍሪካ ወዳጅነትን የመገንባት ውጥን ስኬታማ እንደሚሆን ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እና ቻይና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1970 መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። የሀገራቱ የሁለትዮሽ ትብብር በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂካዊ አጋርነት የተሸጋገረው እ.አ.አ በ2023 ነበር። የሀገራቱ ግንኙነት ወደዚህ ከፍተኛ የዲፕሎማሲ ደረጃ ማደጉ ይፋ የተደረገው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቤጂንግ ከተካሄደው ሶስተኛው የቤልት ኤንድ ሮድ (Belt and Road) ጉባኤ ጎን ለጎን ወቅት ከቻይናው ፕሬዚዳንት ሺ ጂንፒንግ ጋር ባደረጉት ውይይት ላይ ነው።
ኢትዮጵያ የግብርና ምርቷን ለማሳደግ በዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ላይ በትኩረት እየሰራች ነው
Aug 21, 2026 262
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ የግብርና ልማትን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ በመስኖ ልማት፣ በተሻሻሉ ምርጥ ዘሮችና በግብርና ሜካናይዜሽን ላይ በትኩረት እየሰራች መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ ገለጹ። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለስልጣን (ኢጋድ) አባል ሀገራት አምባሳደሮች ኮሚቴና የኢጋድ ፓርላማ ፎረም በአግሪፉድ ሲስተም ዙሪያ በአዲስ አበባ ያዘጋጁት ከፍተኛ የልምድ ልውውጥ መድረክ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ እንደገለጹት ኢትዮጵያ የግብርና ልማትን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ በመስኖ ልማት፣ በተሻሻሉ ምርጥ ዘሮችና በግብርና ሜካናይዜሽን ላይ በትኩረት እየሰራች ነው። የክላስተር እርሻ ልማት አርሶ አደሮች የግብዓት፣ የቴክኖሎጂ፣ የባለሙያ ምክክር አገልግሎትና የገበያ ትስስሮችን በተሻለ ሁኔታ እንዲያገኙ እያስቻለ መሆኑን ጠቁመዋል። በተጨማሪም በአረንጓዴ ዐሻራ እና በሌማት ትሩፋት ተነሳሽነቶች የአካባቢ ጥበቃን፣ የግብርና ምርታማነትንና የቤተሰብ ምግብና የአመጋገብ ስርዓትን ለማሻሻል ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። የኢጋድ ዋና ጸሐፊ ተወካይና በድርጅቱ የውጭ አገልግሎት ኢንስቲትዩት ዳይሬክተር ኦማር ጃማ የአግሪፉድ ሲስተም ለውጥ የካምፓላ የግብርና ልማት ቃል ኪዳንን ወደ ተግባር በማሸጋገር፣ በጠንካራ ፖሊሲ፣ የሕግ ማዕቀፍ፣ በጀትና ኢንቨስትመንት በመደገፍ እንደሚሳካ ጠቁመዋል። ሀገራቱ ለምግብ ዋስትና ችግር፣ ለአየር ንብረት ለውጥ፣ ለዝቅተኛ ምርታማነትና ለውስን የገበያ ትስስር የተጋለጡ በመሆኑ፣ የግብርና ለውጥን ለማፋጠን አባል ሀገራት የተቀናጀ ቀጣናዊ ትብብርን ማጠናከር ይገባቸዋል ብለዋል። በመድረኩ የአግሪፉድ ሲስተም ልማትን ለማፋጠን የፖሊሲ ቅንጅትን፣ የግብርና ኢንቨስትመንትን፣ የቀጣናዊ ንግድ ትስስርንና የፓርላማ ክትትልን ማጠናከል በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ውይይት እየተካሄደ ይገኛል።
አረንጓዴ አሻራ ከአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ጋር መቀናጀቱ ውጤታማ አድርጎናል-አርሶ አደሮች
Aug 21, 2026 196
ገንዳውሃ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ከአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ጋር በማቀናጀት ተጠቃሚ መሆናቸውን የዞኑ አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የቆላ ፍራፍሬ ልማትን በኩታ ገጠም እርሻ ለማልማት ትኩረት ተሰጥቶ እየተከናወነ ይገኛል። በልማቱ ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል አርሶ አደር ደሴ ባይተኩስ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ከአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ጋር አስተሳስረው በመስራታቸው አመርቂ ውጤት አግኝተዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ያለሙትን ሙዝና ማንጎ ለገበያ በማቅረብ ከ150 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ነው የሚናገሩት። በተለይ "በክላስተር መደራጀታችን የውሃ አጠቃቀማችንን እና የግብዓት አቅርቦት ችግራችንን አቃልሎልናል" ያሉት አርሶ አደሩ፣ በዘንድሮው ዓመትም የተሻለ ምርት ለማግኘት እየሰሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሌላኛዋ የወረዳው ነዋሪ አርሶ አደር ፀጋነሽ ብዙነህ በበኩላቸው፥ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተግባራዊ መደረጉ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት በስፋት ለመሳተፍና ተጠቃሚ ለመሆን የሚያስችል ዕድል ይዞ መምጣቱን ገልጸዋል። ሁለት ሄክታር በሚጠጋ መሬት ካለሙት ሙዝ፣ ማንጎና ፓፓያ ከእለት ፍጆታ በተጨማሪ ለገበያ የሚተርፍ ምርት በማምረት ከ100 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ገልጸዋል። የምዕራብ ጎንደር ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ እንዳሉት፥ በዞኑ በ1 ሺህ 113 ሄክታር መሬት ላይ የቡናና የቆላ ፍራፍሬ ልማት እየተካሄደ ይገኛል። ከዚህ ውስጥ 200 ሄክታሩን በክላስተር በፓፓያና በሙዝ ለማልማት በተጀመረው ስራ እስካሁን ከ40 ሄክታር በላይ መሬት መሸፈኑን ገልጸዋል። የፓፓያና የሙዝ ክላስተር ልማትን ይበልጥ ለማስፋፋት መምሪያው ልዩ ትኩረት መስጠቱን የጠቀሱት ኃላፊው፥ አስፈላጊው ግብዓት በወቅቱ ለአርሶ አደሮች እንዲሰራጭ መደረጉን ተናግረዋል።
የማዕድን ዘርፉን የወጪ ንግድ ከማሳደግ ባለፈ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት የመተካቱ ስራ ይጠናከራል
Aug 21, 2026 132
ሃዋሳ ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ) ፦ በበጀት ዓመቱ የማዕድን ዘርፉን የወጪ ንግድ ገቢ ከማሳደግ ባለፈ ከውጭ የሚገባውን የኢንዱስትሪ ግብዓት የመተካቱ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የማዕድን ሚኒስቴር አስታወቀ። በማዕድን ሚኒስቴር የማዕድን ዘርፍ ሚኒስቴር ዴኤታ አቶ ብርሃኔ ያዴሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ከአምስቱ ዋና ዋና የኢኮኖሚ ምሰሶዎች አንዱ ከሆነው የማዕድን ዘርፍ ኢትዮጵያ ተገቢውን ጥቅም እንድታገኝ የተከናወኑ የለውጥ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል። ዘርፉ የሚያስገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግ በተደረገ ተቋማዊ ሪፎርም የማዕድን መረጃዎችን በዘመናዊ መልክ በማደራጀት መረጃን መሠረት ያደረገ የማዕድን አመራር ሥርዓት ተዘርግቷል ብለዋል። የማዕድን ፍለጋዎችንና ሳይንሳዊ ሥራዎችን ከማጠናከር ባለፈ፣ ማበረታቻዎችንና ምቹ መደላድሎችን በመፍጠር ዘርፉ የኢኮኖሚው ሞተር እንዲሆን የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውንም ገልጸዋል። በመሆኑም በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመትም በሀገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያ የሆነውን 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር የወጪ ንግድ ገቢ ከማዕድን ማግኘት ተችሏል ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ከወርቅ በተጨማሪ በተመረጡ የማዕድን ዘርፎች ላይ በማተኮር የዘርፉን የወጪ ንግድ ገቢ 6 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ግብ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ወርቅ ላይ ብቻ የተንጠለጠለውን የወጪ ንግድ ገቢ ለማስፋት፣ ዓለም አቀፍ ፍላጎትን መሠረት በማድረግ በጌጣጌጥና በሌሎች የተመረጡ ማዕድናት ላይ በማተኮር ገቢን የማሳደግና ዘላቂነትን የማረጋገጥ ሥራዎች ይከናወናሉ ብለዋል። በተኪ ምርት ረገድም ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ከውጭ የሚገቡ ማዕድናትን በሀገር ውስጥ የመተካት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፣ አንዳንድ ተኪ ምርቶችን ወደ ውጭ የመላክ ዕቅድ የተያዘበት ዓመት መሆኑንም ገልጸዋል። የሲዳማ ክልል ማዕድንና ኢነርጂ ኤጀንሲ ሥራ አስኪያጅ አቶ መስፍን መጩካ በበኩላቸው፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የማዕድናት ልየታ ሥራ በትኩረት መከናወኑን ገልጸዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 1 ሺህ 350 ኪሎ ግራም ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ መግባቱንና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ከ11 ሺህ ቶን በላይ ማዕድናት ለማዕከላዊ ገበያ መቅረባቸውን ተናግረዋል። በኮንስትራክሽን ማዕድናትም የሕብረተሰቡን ፍላጎት የሚያሟሉ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካት የሚያስችሉ የማርብልና ግራናይት ማዕድናት ወደ ምርት የማስገባት ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። በክልሉ በጥናት የተለዩ ከ22 በላይ ማዕድናት መኖራቸውን የገለጹት ደግሞ በኤጀንሲው የማዕድን ሀብት ዳይሬክተር ወ/ሮ ምርትነሽ መኮንን ናቸው። ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማሳደግም በወርቅ፣ ኮንስትራክሽንና ኢንዱስትሪ ማዕድናት ላይ የተሰማሩ ከ320 በላይ ማኅበራት የገበያ ትስስር እንደተፈጠረላቸው ገልጸዋል። በማርብልና ግራናይት የኢንቨስትመንት ፈቃድ ተሰጥቶ ወደ ምርት ለመግባት የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ከዩናይትድ ኪንግደም ጋር የዓለም ንግድ ድርጅት የሁለትዮሽ ገበያ ዕድል ስምምነት ተፈራረመች
Aug 20, 2026 365
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ከዩናይትድ ኪንግደም ጋር በዓለም ንግድ ድርጅት (WTO) አባልነት ሂደት ማዕቀፍ ስታካሂድ የቆየችውን የሁለትዮሽ የገበያ ዕድል ድርድር በስኬት በማጠናቀቅ የስምምነት ሰነድ ተፈራርማለች። የስምምነት ሰነዱን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባልነት ዋና ተደራዳሪ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር እና በኢትዮጵያ የዩናይትድ ኪንግደም አምባሳደር ዳረን ዌልች ተፈራርመውታል። በፊርማ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ይህ ታሪካዊ ስምምነት የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም እና የፖሊሲ ምህዳር ሙሉ በሙሉ ባስጠበቀ መልኩ የተከናወነ ነው ብለዋል። አክለውም ስምምነቱ የሁለቱን ሀገራት የቆየ ዲፕሎማሲያዊ፣ የንግድ እና የኢንቨስትመንት ትስስር ይበልጥ የሚያጠናክር ከመሆኑም በላይ፣ ኢትዮጵያ በዓለም ንግድ ድርጅት ሙሉ አባል ለመሆን የምታደርገውን ጥረት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ወሳኝ ስኬት መሆኑን አብራርተዋል። የዩናይትድ ኪንግደም አምባሳደር ዳረን ዌልች በበኩላቸው፤ የተደረገው ስምምነት የሁለቱን ሀገራት የቆየ የኢኮኖሚና የዲፕሎማሲ ግንኙነት ይበልጥ የሚያጎለብት መሆኑን ገልጸዋል። ዩናይትድ ኪንግደም ኢትዮጵያ ወደ ዓለም ንግድ ድርጅት ለመቀላቀል የምታደርገውን ጥረት እና የምታካሂዳቸውን የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች በሙሉ ቁርጠኝነት መደገፏን የምትቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ እስካሁን ባለው ሂደት ከቻይና፣ ሩሲያ፣ አርጀንቲና፣ ቱርክ፣ ብራዚል፣ ጃፓን፣ ሕንድ፣ ኒውዚላንድ እና ታይላንድ ጋር ተመሳሳይ ስምምነቶችን ተፈራርማለች። ዩናይትድ ኪንግደም ስምምነቱን በይፋ ከፈረሙ አባል ሀገራት 10ኛዋ እና ድርድሩን በስኬት ካጠናቀቁት ደግሞ 11ኛዋ አባል ሀገር ሆናለች።
ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝ ሀብቷን ለማልማት ከማንም ፈቃድ አያስፈልጋትም - የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር)
Aug 20, 2026 326
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዓባይ ወንዝ ሀብቷን የመጠቀም እና የማልማት ሉዓላዊ መብት ስላላት ከማንም አካል ፈቃድ መጠየቅ እንደማያስፈልጋት የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስትሩ አክለውም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ኤሌክትሪክ ኃይል በማመንጨት ለቀጣናው የሚተርፍ ሀብት መሆኑንም አመልክተዋል። ሚኒስትሩ ከፐልስ ኦፍ አፍሪካ (The Pulse of Africa) ጋር ባደረጉት ቆይታ፣ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የተገነባው ለኃይል ማመንጨት ብቻ እንደሆነና አዎንታዊ ሚናውን ቀጣናዊ የኤሌክትሪክ ግብይትን በማስፋት ከኢትዮጵያ ድንበር የተሻገረ ጠቀሜታ እንዳለውም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለጎረቤት ሀገራት ማለትም ለጅቡቲ፣ ለኬንያ እና ለሱዳን የኤሌክትሪክ ኃይል በማቅረብ ላይ እንደምትገኝ የጠቆሙት ሚኒስትሩ፣ ከሶማሊያ እና ከደቡብ ሱዳን በኩል ያለው የኢነርጂ ፍላጎት በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱንም አብራርተዋል። የዓባይ ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነት (CFA) እና የዓባይ ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ የወንዙን የጋራ ጥቅም ለማሳደግ የተደረጉ ጥረቶች ማሳያ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በሌሎች ድንበር ተሻጋሪ የዓለም ወንዞች ላይ ባለው ተሞክሮ ትብብርን የሚጀምሩት የታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ቢሆኑም፣ በዓባይ ጉዳይ ግን እንተባበር በማለት ውይይቱን በግንባር ቀደምትነት ስትመራ የቆየችው ኢትዮጵያ መሆኗን አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ከሕዳሴ ግድብ በታች የሚገኙ ሊለሙ የሚችሉ መሬቶቿን ከመስኖ ልማት ውጪ ማድረጓ ለታችኞቹ የተፋሰሱ ሀገራት ያላትን ትልቅ ግምት እንደሚያሳይ ሚኒስትሩ አክለው ገልጸዋል። በቴክኒክ ደረጃ፣ ከግድቡ በታች ከ230 ሺህ ሄክታር በላይ የመስኖ ልማት የሚሆን መሬት አለን፤ ነገር ግን በታችኛው ተፋሰስ በኩል ያለውን ፍላጎት ስለምናውቅ ይህንን አላደረግነውም ሲሉ አስረድተዋል። ሚኒስትሩ የህዳሴ ግድብ ኃይል ካመነጨ በኋላ የሚለቀቀው ውሃ ቀጥታ ወደ ታችኛው ተፋሰስ ወደሚገኙ ወንድም ሀገራት እንደሚፈስ በመግለጽ ኢትዮጵያ ለጋራ ተጠቃሚነት ያላትን ቁርጠኝነት አንስተዋል። ሚኒስትሩ ሕዳሴ ግድብን በጋራ ለማስተዳደር የሚቀርቡ ጥሪዎችን ውድቅ ያደረጉ ሲሆን፣ ኢትዮጵያ ሌሎች ሀገራት በግድቡ ላይ ቁጥጥር የሚደረጉበትን አሰራርን አትቀበልም ብለዋል። በኢትዮጵያውያን ገንዘብ የተገነባውን፣ ኩራታችን እና ብሔራዊ የክብር ፕሮጀክታችን የሆነውን ግድብ፣ ግንባታውን ሲቃወም የነበረ አካል መጥቶ በጋራ እናስተዳድር እንዴት ሊል ይችላል? ሲሉ ጠይቀዋል። ይህ ፈጽሞ የማይቻል፣ በፍፁም ሊታሰብ የማይችል ነው ሲሉም ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የዓባይ ተፋሰስ ሀገራት የኢትዮጵያን የልማት መብት ለመገደብ ከመጣር ይልቅ በውይይት እና በትብብር ላይ ትኩረት ማድረግ አለባቸው የሚል የጸና አቋም እንዳላት ተናግረዋል።
በመዲናዋ የተገነቡ የመዝናኛ ፓርኮች አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን ከዘመናዊ የቱሪዝም መስህቦች ጋር አስተሳስራ እንድትቀጥል አስችለዋታል
Aug 20, 2026 376
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦በመደመር መንግሥት በመዲናዋ የተገነቡት የመዝናኛ ፓርኮች አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን ከዘመናዊ የቱሪዝም መስህቦች ጋር አስተሳስራ እንድትቀጥል ማስቻላቸውን የአንድነት ፓርኮች ኮርፖሬሽን ገለጸ። በመዲናዋ የተገነቡት ፓርኮች ልዩ ልዩ ሁነቶችን ማከናወን የሚያስችሉ መሰረተ ልማቶች የተሟላላቸው እና ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠር ማስቻላቸውም ተመላክቷል። የመደመር መንግሥት ቱሪዝምን አንዱ የኢኮኖሚ ምሰሶ በማድረግ በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገር እና ገበታ ለትውልድ ተነሳሽነቶች አማካኝነት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ዘመናዊ የቱሪስት መዳረሻዎችን ገንብቷል። እነዚህ ግዙፍ የቱሪዝም መዳረሻ የልማት ሥራዎች የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎችን ቀልብ በመሳብ ኢትዮጵያን ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ በማድረግ ከዘርፉ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ አስችለዋታል። በገበታ ለሸገር ከተገነቡት የቱሪዝም መዳረሻዎች መካከል የአንድነት ፓርክ የመዲናዋን ማራኪነት በማጎልበት በጎብኚዎች ተመራጭ እንድትሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ወዳጅነት ፓርክ አንድ እና ሁለት አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ገጽታዋን ከዘመናዊ ቱሪዝም ጋር አጣጥማ እንድታስቀጥል ምቹ ዕድል ፈጥረዋል። የአንድነት ፓርኮች ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ሥራ አስፈፃሚ ነጃት ግርማ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ ፓርኮቹ ባለፉት ዓመታት በርካታ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ጎብኚዎችን መሳብ ችለዋል። የፓርኮቹ ተገንብቶ አገልግሎት መስጠት ለበርካታ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም ተናግረዋል። በተጨማሪም ፓርኮቹ የተለያዩ ሁነቶችን በማስተናገድ ከፍተኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እንዲፈጠር ማስቻላቸውን ጠቁመዋል፡፡ ይዘት ፈጣሪዎች ሥራዎቻቸውን የሚያከናውኑበት ተመራጭ ማዕከል መሆን መቻላቸውን ጠቅሰው፤ የተለያዩ የንግድ ተቋማት በፓርኩ ሥራቸውን በተሻለና ምቹ በሆነ መልኩ እንዲያከናወኑ ማድረጉን ተናግረዋል። ይህም የኢኮኖሚ ፍሰቱን በማሳለጥ በኩል አወንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በፓርኩ ሲዝናኑ ያገኘናቸው ወጣቶች በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በቱሪዝም ዘርፍ ያላትን እምቅ አቅም ለመጠቀም እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የሚደነቁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል ናሆም ተስፋዬ፣ በአሁኑ ወቅት የአንድነት ፓርክን ጨምሮ በተለያዩ አካባቢዎች በርካታ የቱሪዝም መሠረተ ልማቶች መገንባታቸው በርካታ ጠቀሜታ እንዳላቸው ተናግሯል፡፡ ይህም ለሀገር ውስጥና ለውጭ ጎብኚዎች መሳብ እንዲሁም የኢትዮጵያን ገጽታ በመገንባት በኩል አበርክቷቸው ከፍተኛ መሆኑን ጠቁሟል፡፡ በመዲናዋ የተገነቡ እና እየተገነቡ የሚገኙ የቱሪስት መስህብ ስፍራዎች ለከተማዋ የቱሪዝም ዘርፍ መነቃቃት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን የገለጸችው ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ቤዛ ክፍሌ ናት፡፡ በከተማዋ የተገነባው የአንድነት ፓርክም ለጎብኚዎች ምቹ እና ተመራጭ የመዝናኛ ስፍራ ከመሆን ባለፈ ለቱሪዝም እድገት የራሱን ከፍተኛ ሚና እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጻለች፡፡ ሌላው አስተያየት ሰጪ ወጣት ሀንደሰ ዓለሙ በበኩሉ፣ አንድነት ፓርክ ለወጣቶች የስራ ትስስር እና የሀሳብና ልምዶችን የሚጋሩበት ምቹ አውድ መፍጠሩን ገልጿል፡፡
አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን እያደገ መጥቷል- አርሶ አደሮች
Aug 20, 2026 180
መተማ፣ ነሐሴ14/2018 (ኢዜአ):- አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን የምዕራብ ጎንደር ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የቆላ ፍራፍሬ ልማትን በኩታ ገጠም አሠራር በሰፊው በማልማት አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታውቋል። አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አትክልትና ፍራፍሬዎችን በኩታ ገጠም በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን እያደገ መጥቷል። በዞኑ የመተማ ወረዳ አርሶ አደር ደሴ ባይተኩስ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መምጣት በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል። ባለፉት ዓመታት ካለሙት ሙዝና ማንጎ ልማት ብቻ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ150 ሺህ ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘታቸውንም ገልጸዋል። "በተለይም በክላስተር በመደራጀታችን የውኃ አጠቃቀማችንና የግብዓት አቅርቦታችንን ለማስተካከል አስችሎናል" ያሉት አርሶ አደሩ፣ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በስፋት የፍራፍሬ ችግኞችን መትከላቸውን ተናግረዋል። በወረዳው የመንደር 6 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ፀጋነሽ ብዙነህ በበኩላቸው፣ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት በመሳተፋቸው ተጨማሪ ገቢ ማግኘት እንደቻሉ ገልጸዋል። እስካሁን ሁለት ሄክታር የሚጠጋ መሬትን በሙዝ፣ በማንጎና በፓፓያ ማልማታቸውን ጠቁመው፣ ምርቱን ለቤት ውስጥ ፍጆታ ከማዋል ባሻገር የተረፈውን በመሸጥ በዓመት ከ100 ሺህ ብር በላይ ገቢ እንደሚያገኙ አስረድተዋል። አርሶ አደር ፀጋነሽ አክለውም፣ የአረንጓዴ ልማቱ የመሬቱን ለምነት በመጨመር ከሰብል ልማት በተጨማሪ በፍራፍሬ ልማትም ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረጉን ጠቁመው፣ ያገኙትን ውጤት ለማስቀጠል እንደሚተጉም ገልጸዋል። የምዕራብ ጎንደር ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አንዳርጌ ጌጡ እንደገለጹት፣ በዞኑ በ1 ሺህ 113 ሄክታር መሬት ላይ ቡናና የቆላ ፍራፍሬ የማልማት ሥራ እየተካሄደ ይገኛል። እስካሁን 117 አልሚ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማቱ በኩታ ገጠም እየተካሄደ እንደሚገኝ ጠቁመው፣ በዚሁ አሠራር ከ40 ሄክታር በላይ መሬት በፓፓያና በሙዝ ለምቷል ብለዋል። የምዕራብ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ በአሁኑ ወቅት እየታየ ያለውን አዎንታዊ ውጤት ከአረንጓዴ አሻራ ልማቱ ጋር ይበልጥ በማስተሳሰር የማስፋፋት ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጧል።
የእንሰት ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረጉ የምርምር ሥራዎች ይጠናከራሉ
Aug 20, 2026 144
ወልቂጤ፣ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡-የእንሰት ተክልን ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት አስታወቀ፡፡ እንሰት ለብዙ ኢትዮጵያውያን የዕለት ተዕለት የምግብ ዋስትና መሠረት በመሆኑ በእንሰት ላይ የሚካሄዱ የምርምር ሥራዎች በሽታን በመቋቋም ምርታማነትን የማሳደግ እና ባህላዊ አሰራርን የማዘመን ጠቀሜታው አላቸው። በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የግብርና ምርምር ማስተባበሪያ ጽህፈትቤት ሃላፊ መኩሪያ ታደሰ (ዶ/ር) እንዳሉት የእንሰት ልማት ከአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ ጋር በማጣጣም እየተከናወነ ይገኛል። ልማቱ የህብረተሰቡን የምግብ ዋስትንና ለማረጋገጥ እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በሚያስችል መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጡ የተሻሻሉ የእንሰት ዝርያዎች ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። በእንሰት ልማት ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንና በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በግብርና ሚኒስቴር የሥራ ሥርና እንሰት ልማት ዴስክ ኃላፊ አቶ ጉቱ ሚጀና እንደገለጹት፣ የእንሰት ልማትን ከአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጋር በማጣጣም እየተከናወነ ይገኛል። እንሰት ከፍተኛ የምግብ ምርት የሚሰጥ፣ ድርቅን የሚቋቋም እና የአፈር እርጥበትን የመጠበቅ ተፈጥሯዊ ባህሪ ስላለው ለአረንጓዴ ልማት ሥራው ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል። የእንሰት ተክልን ምርታማነት ለማሳደግ በምርምር የተደገፈ ሥራ እየተከናወነ መሆኑንም አመልከተዋል። የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተርና ተመራማሪ አቶ ቤተል ነክር ማዕከሉ በበኩላቸው፣ በሽታን ተቋቁመው የተሻለ ምርት የሚሰጡ አዳዲስ የእንሰት ዝርያዎችን በስፋት አባዝቶ ለአርሶ አደሩ እያሰራጨ መሆኑን ተናግረዋል። እንሰት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ብቻ በመጠቀም እንደሚለማ ገልጸው፣ ከአካባቢው አርሶ አደሮችና ሌሎች የምርምር ተቋማት ጋር በመቀናጀት ውጤታማ ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። እንሰት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የአየር ንብረትን ለማስጠበቅና የአፈር እርጥበትን ለመጠበቅ ጠቀሜታ እንዳለው የገለጹት ደግሞ የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ ናቸው። ከምግብ ፍጆታነት ባለፈ የአርሶ አደሩ የገቢ ምንጭ እንዲሆንና ከተረፈ ምርቱም የተሻለ ጥቅም ለማግኘት የተሰሩ ሥራዎች ውጤት እያመጡ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በጉራጌ ዞን የእዣ ወረዳ አርሶ አደር ጀማል ሁሴን እና ወይዘሮ ነፃነት አርጋ በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የእንሰት ችግኞች በማግኘታቸው የተዳከመውን የእንሰት ልማት ሥራቸውን ለማጠናከር መቻላቸውን ገልጸዋል። ከዚህ በፊት ለእንሰት ተክል ብዙም ትኩረት እንደማይሰጡ አስታውሰው፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተሻሻሉ የእንሰት ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማ መሆን መቻላቸውን ተናግረዋል፡፡ የእንሰት ምርታማነትንና ተደራሽነትን ለማሳደግ በሚከናወኑ ተግባራት ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውንም አመልክተዋል።
የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነትን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በቅንጅት የተከናወነው ተግባር ውጤታማ ነው
Aug 20, 2026 135
ደሴ፤ ነሐሴ 14/2018(ኢዜአ)፡- በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነትን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በቅንጅት የተከናወነው ተግባር ውጤታማ መሆኑን በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የደሴ ሪጅን ገለጸ። የሪጅኑ ዳይሬክተር አቶ ሀብቱ አበበ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኤሌክትሪክ ኃይል ተደራሽነትን በማስፋት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በቅንጅት የተሠራው ሥራ ውጤታማ ነው። በዚህም በደሴ፣ በደቡብ ወሎ፣ በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር፣ በኮምቦልቻና አካባቢዋ 29 ሺህ 191 አዳዲስ ደንበኞችን የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ የተከናወነው ተግባር ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ9 ሺህ ደንበኞች ብልጫ እንዳለው የጠቆሙት ዳይሬክተሩ፣ ይህም በቅንጅትና በትብብር በመሥራት የመጣ ውጤት መሆኑን አስረድተዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም ከ43 ሺህ በላይ አዳዲስ ደንበኞችን የኤሌክትሪክ ኃይል ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ኅብረተሰቡም በአካባቢው የሚገኙ የኤሌክትሪክ ምሰሶዎችን፣ መስመሮችን፣ ትራንስፎርመሮችንና ሌሎች የመሠረተ ልማት አውታሮችን በንቃት እንዲጠብቅም አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የደሴ ሪጅን ከ250 ሺህ በላይ ደንበኞች እንዳሉት ከሪጅኑ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የሙዝ ምርት በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነቱን ለማሳደግ የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት ወሳኝ ነው
Aug 20, 2026 387
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፦ የሙዝ ምርትን በዓለም አቀፍ ገበያ ያለውን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የጥራት ማሻሻያና የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት ወሳኝ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ አበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ አምራች ላኪዎች ማህበር የሙዝ ወጪ ንግድ ላይ ያተኮረ ሀገር አቀፍ ጉባዔ እያካሄደ ይገኛል፡፡ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የሙዝ ምርት መጠን ቢኖርም ለውጭ ንግድ የሚቀርበው ለጎረቤት ሀገራት ብቻ ነው። ኢትዮጵያ ያላትን ለግብርና የተመቹ አግሮ-ኢኮሎጂያዊ ሁኔታዎች ወደ ሀብትና ካፒታል በመቀየር ዓለም አቀፍ የገበያ መዳረሻዎችን ማስፋት ይገባል ብለዋል። የመንግሥትና የግሉ ዘርፍ ትብብር በሆርቲካልቸር ዘርፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ ማድረጉን በማንሳት፤ በአትክልትና ፍራፍሬ ያለውን ተቋማዊ ልምድ፣ የሎጂስቲክስ እውቀት እና ዓለም አቀፍ የገበያ ትስስር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ሚኒስቴር ዘርፉን ገበያ ተኮር፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገርና ዘላቂ ለማድረግ በርካታ የፖሊሲ እና የስትራቴጂ ማዕቀፎችን ቀርጿል ብለዋል። የኢትዮጵያን ሆርቲካልቸር ዘርፍ ለማሳደግ የ10 ዓመት ብሔራዊ የሆርቲካልቸር ስትራቴጂ በመቅረጽ ለዘርፉ እድገት በቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም የሙዝ ምርት ዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የጥራት ማሻሻያና የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። በአበባና በአትክልት ዘርፍ የተገነባው ተቋማዊ ልምድ፣ የሎጂስቲክስ እውቀት እና ዓለም አቀፍ የገበያ ትስስር ለሙዝ ኢንዱስትሪው ስኬት መጠቀም ይገባልም ብለዋል። የኢትዮጵያ አበባ አትክልትና ፍራፍሬ አምራች ላኪዎች ማህበር ዋና ዳይሬክተር ቴዎድሮስ ዘውዴ፤ በሆርቲካልቸር ኢንዱስትሪ ዘርፍ ያለውን እምቅ አቅም ለመጠቀም ከግብርና ሚኒስቴር እና ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየሠሩ መሆኑን ገልጸዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ በብዛት ከሚመረቱ የፍራፍሬ ዝርያዎች አንዱ መሆኑን ገልጸው፤ በኢትዮጵያ ከምግብነት ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የገቢ ምንጭና ሥራ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል ከ18 ሺህ 800 ካሬ ሜትር በላይ የከተማ መሬት ወደ መሬት ባንክ እንዲገባ ተደርጓል
Aug 20, 2026 133
አዳማ ፤ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ከ18 ሺህ 800 ካሬ ሜትር በላይ የከተማ መሬት ወደ መሬት ባንክ እንዲገባ መደረጉን የክልሉ ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አስታወቀ። የክልሉ ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር አብደላ ኦገቴ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተለያዩ ሴክተሮች ሙስና እና ብልሹ አሰራሮችን ለመከላከል የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራትን አንስተዋል። በክልሉ በመንግስት ተቋማት የሚስተዋሉ ብልሹ አሰራሮችን አስቀድሞ ለመከላከል የሚያስችሉ 26 የሙስና መከላከል የአሰራር ስርዓት ጥናቶች መካሄዳቸውን ዘርዝረዋል። የመስኖ ፕሮጀክት ግንባታና የውል አስተዳደር፣ የሕገ-ወጥ ንግድ ክትትል እና የገቢ አሰባሰብ ስርዓት፣ የግል ህክምና ተቋማት የፈቃድ አሰጣጥና ክትትል፣ የአርሶ አደሮች ህብረት ሥራ ማህበራትና ዩኒየኖች የግዥና ሽያጭ አሰራር ጥናቶች የሚገኙበት መሆኑን ጠቅሰዋል። በተለይም በመሬት ሃብት ላይ የሚደርሰውን ምዝብራ ለመከላከል ብዙ ጥረት መደረጉን አስታውሰው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 18 ሺህ 849 ካሬ ሜትር የከተማ መሬት ወደ መሬት ባንክ ተመላሽ ተደርጓል ብለዋል። በዚህም የከተማ መሬትን ከህገ-ወጥ ወረራ፣ ከደላሎች ድብቅ ሽያጭ እና ከአሰራር ብልሹነት በመታደግ ወደ "መሬት ባንክ" ማስገባት፤ መሬቱ ለታለመለት ልማት እንዲውል ማድረግ እየተቻለ ስለመሆኑ አንስተዋል። በተጨማሪም በየደረጃው ለሚገኙ 6 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎች ግንዛቤ ለማስጨበጥ ታቅዶ፤ ከ10 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑት ተደራሽ በማድረግ ከእቅድ በላይ ማሳካት ስለመቻሉ ተናግረዋል። የሙስና ወንጀል ህጎች፣ የግዥና ግንባታ አስተዳደር ውል ህጎች፣ የሀብት ማስመለስ አዋጅ፣ የሙያ እና የአመራርነት ሥነ-ምግባር እንዲሁም የመከላከል ስትራቴጂዎች ላይ በማተኮር ግንዛቤ ስለመሰጠቱም አስታውሰዋል። ከ135 ሺህ በላይ የህዝብ ተመራጮች፣ ተሿሚዎች እና የመንግስት ሰራተኞች በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ የሃብት ምዝገባ ስራ ስለመካሄዱም ገልጸው በተያዘው ዓመትም መሰል ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። በሀገሪቷ በወጣው የሀብት ማስታወቂያና ምዝገባ አዋጅ ቁጥር 668/2002 መሠረት ተሿሚዎችና የመንግስት ሰራተኞች ሀብታቸውን እንዲያስመዘግቡ የሚደነግግ መሆኑ ይታወቃል።
የሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር ዘላቂ ተጠቃሚነታችንን ለማረጋገጥ አስችሎናል-አርሶ አደሮች
Aug 20, 2026 151
ደብረብርሃን፤ ነሀሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡-በሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር በመሳተፍ ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ መቻላቸውን አርሶ አደሮች ገለጹ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የቤተሰብንና የሀገርን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ፣ የስነ-ምግብ አቅርቦትን ለማሻሻል እና የዜጎችን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት ተግባራዊ የተደረገ ወሳኝ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው። መርሃ ግብሩ በዋናነት የእንስሳት እና የዶሮ እርባታን፣ የወተት ምርትን፣ የ ማር እና የዓሣ ሀብት ልማትን በማስፋፋት አነስተኛ የቤት ውስጥ ምርታማነትን ወደ ላቀ የገበያ መር ምርት ማሸጋገርን ዓላማ ያደርጋል። በደብረብርሃን ከተማ አስተዳደር የባቄሎ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሰለሞን ሽፈራው ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ለወተት ልማት ዘርፉ ልዩ ትኩረት በመስጠቱ በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ ለመሆን አስችሎናል። በተለይም ዝርያቸው የተሻሸሉ የወተት ላሞችን በማራባት ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እንደቻሉ ነው የሚናገሩት። በተለይ የእንስሳት መኖ አቅርቦትና የአመጋገብ ሥርዓቱ እየተሻሻለ በመምጣቱ ከአንድ ላም በቀን በአማካይ 20 ሊትር ወተት ማግኘት ማስቻሉን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት በቀን ከ50 ሊትር በላይ ወተት ለሕብረት ሥራ ማህበራቸው በማቅረብ የተሻለ ገቢ እያገኙ መሆኑን ነው የጠቆሙት። በዚህም መኖሪያ ቤታቸውን ከማዘመን ባለፈ ገንዘብ ለመቆጠብና ሀብት ለማፍራት እንደቻሉ ገልጸዋል። በተመሳሳይ በከተማ አስተዳደሩ የወሻውሽኝ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ጌታሁን ገነነ በበኩላቸው፣ ቀደም ሲል ከነበሯቸው የሀገር ውስጥ ላሞች በቀን ከአራት ሊትር ያልበለጠ የወተት ምርት ያገኙ እንደነበር አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት ግን የላሞችን ዝርያ በማሻሻል፣ በቂ መኖ በማዘጋጀትና የአመጋገብ ሥርዓቱን በማዘመን ከአንድ ላም በቀን እስከ 20 ሊትር ወተት ለማግኝት መቻላቸውን አስረድተዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ የእንስሳትና እንስሳት ተዋጽኦ ግብይት ቡድን መሪ አቶ ዳዊት አሳምነው በበኩላቸው፣ በበጀት ዓመቱ 37 ሚሊዮን 100 ሺህ ሊትር ወተት ለ44 አቀነባባሪዎች ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል። በተጨማሪም የ2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ግምት ያለው የወተትና የወተት ተዋጽኦ ምርት ግብይት በመፈጸም አምራቾችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አብራርተዋል። የተገኘውንም ውጤት በአዲሱ የበጀት ዓመት በማስፋት አርሶ አደሩን ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሠራ እንደሚገኝ አመልክተዋል።
በወልዲያ ከተማ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ11 ሺህ በላይ ለሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል- መምሪያው
Aug 20, 2026 118
ወልዲያ፤ ነሐሴ 14/2018 (ኢዜአ)፡- በወልዲያ ከተማ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ለ11 ሺህ 768 ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻሉን የከተማ አስተዳደሩ ሥራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ መላኩ አለሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የከተማዋን ሰላም ከማረጋገጥ ጎን ለጎን ለወጣቶች የሥራ ዕድል የመፍጠር ተግባር ልዩ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ ነው። በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ለ9 ሺህ 268 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ ከእቅድ በላይ ለ11 ሺህ 768 ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል። ይህም ከዕቅዱ ጋር ሲነጻጸር 127 በመቶ አፈፃፀም ማስመዝገብ እንደተቻለ ነው ያመለከቱት። ከዕቅድ በላይ ማሳካት የተቻለው የአካባቢው ሰላም እየተሻሻለ በመምጣቱና የፖለቲካ አመራሩ ለዘርፉ ልዩ ትኩረት በመስጠቱ መሆኑንም አስረድተዋል። የሥራ ዕድሉ የተፈጠረው በከተማ ግብርና፣ በአምራች ኢንዱስትሪ፣ በብረታ ብረት፣ በአገልግሎትና በሌሎች ዕድገት ተኮር ዘርፎች መሆኑንም አብራርተዋል። ለሥራ ዕድል ተጠቃሚ ወጣቶች የብድር፣ የመሥሪያና የመሸጫ ቦታ (ሼድ) እንዲሁም የገበያ ትስስር ድጋፍ መደረጉንም አብራርተዋል። የስራ እድሉ ተጠቃሚ የሆነች የወልድያ ከተማ ነዋሪ ወጣት እመቤት ደምሴ፤ በተደረገላት ድጋፍ በአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆኗን ገልጻለች። አትክልትና ፍራፍሬ ከመሸጥ ጎን ለጎን እንጀራ በመጋገርና በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኘች መሆኑንና ሥራዋን ለማስፋት ተግታ እየሠራች እንደምትገኝ ተናግራለች። ሌላዋ ወጣት ሸዋዬ ኃይሉ በበኩሏ፤ በተሰጣት የሥልጠና ድጋፍ የወረቀት ቦርሳ በማምረትና ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆኗን ገልጻለች። ከጓደኞቿ ጋር በመደራጀት የጀመረችው ሥራ በየወሩ እስከ 50 ሺህ ብር ገቢ እያስገኘላቸው መሆኑን አስረድታለች። በ2019 በጀት ዓመት ለ11 ሺህ 923 ሥራ አጥ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወደ ሥራ መገባቱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
የህዳሴ ግድብ ለሱዳን አዲስ የኢኮኖሚ እድል የሚፈጥርና የቀጣናዊ ትስስር መንገድ የሚከፍት ነው-ዓለም አቀፍ የውሃ ኤክስፐርት ፕሮፌሰር ሰይፍ አል-ዲን ሀማድ
Aug 20, 2026 286
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፦ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለሱዳን በርካታ የኢኮኖሚና የልማት እድሎችን የሚያስገኝና የቀጣናዊ ትስስር መንገድን ይበልጥ የሚያሰፋ መሆኑን የቀድሞው የሱዳን የውሃ ሀብት ሚኒስትርና ዓለም አቀፍ የውሃ ኤክስፐርት ፕሮፌሰር ሰይፍ አል-ዲን ሀማድ ገለጹ። ፕሮፌሰር ሰይፍ አል-ዲን ሀማድ ከአል-ኒላይን የዜና ቻናል ''ሙቅረን አል-ኒላይን'' ፕሮግራም ጋር ባደረጉት ቃለ-መጠይቅ፤ በወንዝ ላይ በደረጃ (Cascade System) የሚገነቡ ግድቦች የተቀናጀና ዘመናዊ አስተዳደር ከተከተሉ፣የወንዙን የተፈጥሮ ፍሰት በማስተካከልና በማረጋጋት ለተፋሰሱ ሀገራት የጋራ ጥቅም የሚሰጡ እንጂ በምንም አይነት መልኩ ስጋት ሊሆኑ እንደማይችሉ አስረድተዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅ የዓባይ ወንዝ በክረምት ወቅት ብቻ በከፍተኛ መጠን ይፈስ የነበረበትን ሁኔታ በመቀየር፣ዓመቱን ሙሉ የተስተካከለና የተመጣጠነ የውሃ ፍሰት እንዲኖር እንደሚያደርግ አመልክተዋል። ይህም ሁኔታ ለሱዳን በርካታ የኢኮኖሚና የልማት እድሎችን ይዞ እንደሚመጣ አንስተዋል። ከእነዚህ እድሎች መካከል አንዱ የኤሌክትሪክ ማመንጨት አቅምን ማሳደግ ሲሆን፣ የተስተካከለው የውሃ ፍሰት እንደ ሮዛሪስ እና ሴናር ያሉ የሱዳን ግድቦች ያለ ተጨማሪ ወጪና ህዝብ መፈናቀል ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ኃይል እንዲያመነጩ የሚያስችላቸው መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የወንዙ ውሃ ከፍ ማለቱ የሱዳን አባወራዎችና አምራቾች ለግብርና መስኖ ይጠቀሙበት የነበረውን የፓምፕ ወጪ ከ30 እስከ 50 በመቶ ያህል እንደሚቀንስ አስረድተዋል። በተጨማሪም የተስተካከለው የውሃ ፍሰት በሱዳን የውሃ ላይ ትራንስፖርትን እንደገና እንዲያሰራራ ትልቅ እድል እንደሚፈጥር ፕሮፌሰር ሀማድ ገልጸዋል። በሌላ በኩል፣ የሕዳሴው ግድብ ይፈርሳል ወይም የጎርፍ አደጋ ያመጣል በሚል የሚነሱ ስጋቶችን ፕሮፌሰር ሀማድ በሳይንሳዊ ማስረጃ ውድቅ አድርገውታል። ግድቡ ከምስራቅ አፍሪካ ስምጥ ሸለቆ የመሬት መንቀጥቀጥ ቀጠና 600 ኪሎ ሜትር ያህል የራቀ ከመሆኑም በላይ፣ በካሬ ሜትር እስከ 10 ሺህ ቶን መሸከም በሚችል ጠንካራ የግራናይት ድንጋይ ላይ የተገነባ በመሆኑ ምንም ዓይነት የመዋቅር አደጋ የለበትም ብለዋል። እንደ የቀድሞው የሱዳን የውሃ ሀብት ሚኒስትር ፕሮፌሰር ሰይፍ አል-ዲን ሀማድ ገለጻ፤ ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ ላይ የምትገነባቸው አዳዲስ ግድቦች የውሃ አሞላልን አስመልክቶ ቅድመ ስምምነት ላይ ከተደረሰባቸው በሱዳን ላይ ምንም ዓይነት ስጋት አያመጡም። ፕሮፌሰር ሀማድ ሱዳን ከተሳሳቱ ስጋቶችና እርግጠኛ ካልሆኑ ሀሳቦች በመውጣት፣የሕዳሴ ግድብ የፈጠረው አዲስ የውሃ እውነታ ጋር የሚጣጣም ብሔራዊ የውሃ ሀብት ስትራቴጂ ማዘጋጀት እንዳለባት አሳስበዋል። ለዚህም በሀገሪቱ መሪ የሚመራ ብሔራዊ የውሃ ሀብት ምክር ቤት ስራውን አጠናክሮ በመቀጠል የተቀናጀ እቅድ ማውጣት እንዳለበት ጠቁመዋል።
በይርጋዓለም ከተማ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የዶሮ አርቢዎችን ኢኮኖሚያዊ አቅምን እያሳደገ ነው
Aug 19, 2026 327
ይርጋለም፤ ነሀሴ 13/2018 (ኢዜአ)፡-በይርጋዓለም ከተማ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዶሮ እርባታ ሥራ የተሰማሩ ማህበራት ከእንቁላል ምርታቸው ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን ገለጹ። በሲዳማ ክልል ማዕከላዊ ሲዳማ ዞን ይርጋዓለም ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው ማህበራት እንደገለጹት፣ የተሰማሩበት የዶሮ እርባታ ሥራ የእንቁላል ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የኢኮኖሚ አቅማቸውን እያሳደገው ነው። ከእንቁላል ሽያጭ በሚያገኙት ገቢ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱንም ለኢዜአ ገልጸዋል። በከተማው የጌዶሴይ ዶሮ እርባታ ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ከተማ ካቢሶ ሥራውን በ1 ሺህ የእንቁላል ጣይ ዶሮዎች እንደጀመሩ አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ያሏቸው የዶሮዎች ቁጥር 4 ሺህ መድረሱን ተናግረዋል። ከእነዚህም በቀን ከ3 ሺህ 700 በላይ እንቁላል እንደሚሰበስቡና ከሽያጩም የተሻለ ገቢ እያገኙ መሆናችውን አስረድተዋል። ከእንቁላል ምርት ባለፈ የአንድ ቀን ጫጩቶችን በማስመጣትና አሳድገው በ48 ቀናቸው ለተጠቃሚዎች በማስረከብ ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በሥራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ከመንግስት የመስሪያ ቦታ፣ የስልጠናና ሌሎች ድጋፎችን እያገኙ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። የደረሰና ቤተሰቡ የዶሮ እርባታ ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ደረሰ አሰፋ በበኩላቸው "የዶሮ እርባታ ሥራ አስፈላጊ መኖና ሕክምናን ከማሟላት ባለፈ በጥንቃቄ መስራት ከተቻለ ትርፋማ ያደርጋል" ብለዋል። በአንድ ሺህ የእንቁላል ጣይ ዶሮዎች የጀመሩትን ሥራ አስፋፍተው በአሁኑ ወቅት ከ10ሺህ በላይ ዶሮዎች እንዳሏቸው ገልፀዋል፡፡ በቀን ከ9 ሺህ በላይ እንቁላል ለገበያ በማቅረብ ጥሩ ገቢ እያገኙ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ደረሰ፣ በስራቸው ለሌሎቸም የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ነው የተናገሩት ከመንግስት ነጻ የዶሮ ክትባቶችን ጨምሮ የሙያና የተለያየ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑንም ገልፀዋል፡፡ የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ምክትልና የዝርያ ማሻሻልና መኖ ልማት ዘርፍ ኃላፊ አደገ አለሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው በክልሉ በሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር ከተከናወኑ ተግባራት መካከል የዶሮ ልማት ሥራ ትልቅ እመርታ ማሳየቱን ገልጸዋል፡፡ የዶሮ ሀብት ልማት በየቤታቸው የተወሰኑ ዶሮዎችን የሚያረቡ አርሶ አደሮች፣ በማህበር ተደራጅተው የሚሰሩ ዜጎችን እንዲሁም በግል የሚያለሙ ባለሀብቶችን ተጠቃሚ አድርጓል ብለዋል። በዘርፉ ለተሰማሩ ማህበራት እና ዶሮ ፈላጊዎች የዶሮ አቅርቦት፣ የሙያ እገዛና ሌሎች የድጋፍና ክትትል ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ኃላፊው አደገ (ዶ/ር) ጠቁመዋል፡፡ እንደእሳቸው ገለጻ ከአምስት ዓመት በፊት በክልሉ በዓመት ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን በታች የነበረውን የዶሮ ሥርጭት በአሁኑ ወቅት 20 ሚሊዮን ለማድረስ ተችሏል። በተያዘው 2019 በጀት ዓመትም 24 ሚሊዮን ዶሮዎችን ለማሰራጨት ማታቀዱን ጠቁመዋል፡፡
በድሬደዋ በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተሰማሩ አልሚዎችን በመደገፍ የኮንፍረንስ ቱሪዝምን ማሳደግ ተችሏል
Aug 19, 2026 124
ድሬደዋ፤ ነሐሴ 13/2018(ኢዜአ)፦ በድሬደዋ ከተማ አስተዳደር በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተሰማሩ አልሚዎችን በመደገፍ የኮንፍረንስ ቱሪዝምን ማሳደግ መቻሉን የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ አመራር አካላት በሆቴል ኢንቨስትመንት ለመሰማራት ፈቃድ ወስደው ግንባታ ላይ የሚገኙ ባለኮከብ ሆቴሎችን የመስክ ጉብኝት አድርገዋል። ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ አስተዳደሩ የከተማዋን ኢንቨስትመንት ለማስፋፋት የቀየሰው የአሰራርና የህግ ማእቀፍ በርካታ አልሚዎችን ወደ ስራ ማስገባት አስችሏል። ለዚህም የመሠረተ ልማት፣ የመሬት አቅርቦት፣ የውሃ፣ የኤሌክትሪክ፣ የፋይናንስ እና ሌሎች ድጋፎችን ከመስጠት አኳያ ከተቋማት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል። ይህም በተለይም በሆቴሎች ዘርፍ ፈቃድ ወስደው በግንባታ ላይ የነበሩ አልሚዎች ስራቸውን አጠናቀው ወደ አገልግሎት በመግባት የቱሪዝሙን እንቅስቃሴ እያሳደጉ መሆናቸውን አስረድተዋል። ለአብነትም በበጀት አመቱ በግንባታ ላይ የነበሩ አምስት ሆቴሎች ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን አንስተዋል። ይህም ከተማዋን የቱሪዝም ኮንፍረንሰ ማእከል ለማድረግ የተጀመረውን ጥረት ለማሳካትና የቱሪስቶችን ቆይታ ለማራዘም ማገዙን ገልጸዋል ። የዛሬው ጉብኝትም አስተዳደሩ በሆቴል አገልግሎት ዘርፍ የተሰማሩ ባለሃብቶችን ለማበረታታት ያለመ ነው ብለዋል። እንዲሁም በግንባታ ላይ ያሉ ሆቴሎችን በማበረታታት በፍጥነትና በጥራት ወደ አገልግሎት ለማስገባት አቅጣጫ ለማስቀመጥ መሆኑን ጠቅሰዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወንደሰን አባይ አስተዳደሩ ተፈጥሮአዊና ታሪካዊ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማት የዘርፉን ጠቀሜታ ለማጉላት እየሰራ ነው ብለዋል። በዚህም መስህቦቹን ለጎብኚዎች አመቺ የማድረግና ከከተማዋ ኮሪደር ልማት ጋር ተሰናስሎ እንዲሄድ መደረጉን ገልጸዋል። በከተማዋ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶችን ፍሰትና የቆይታ ጊዜ ለማራዘም የቱሪስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ማስፋፋት ላይ ትኩረት መሰጠቱን ጠቁመዋል። በዚህም በተጠናቀቀው በጀት አመት ከ700 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥ እና ከ15 ሺህ በላይ ቱሪስቶች መስህቦቹን መጎብኘታቸውን አስረድተዋል። የከተማዋ የቱሪዝም ልማትም የስራ እድልን ለማስፋትና የከተማውን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ከፍ ማድረጋቸውን አስታውቀዋል። በተያዘው በጀት አመትም በቱሪዝም ዘርፍ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በግንባታ ላይ ከሚገኙ ባለኮኮብ ሆቴሎች ባለቤት አቶ ሱራፌል ሲሳይ በበኩላቸው የከተማ አስተዳደሩ ለዘርፉ የሚያደርገው ድጋፍና ክትትል ስራቸውን ለማቀላጠፍ እያገዛቸው መሆኑን ጠቅሰዋል። በግባታ ላይ የሚገኘው ሆቴልም ለከተማዋ የቱሪስት ፍሰትና ለወጣቶች የስራ ዕድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል።
በአማራ ክልል የአፈር ለምነትን የሚያሻሽል የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል
Aug 19, 2026 141
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 13/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል በበጀት ዓመቱ የአፈር ለምነትን የሚያሻሽል 86 ሚሊዮን ሜትር ኩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደተግባር መገባቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የአፈር ለምነት ባለሙያ አቶ አምሳሉ አድማስ ለኢዜአ እንደገለጹት በአሲድ የተጠቃ አፈር ለምነትን ለመመለስና የሰብል ምርታማትን ለማሳደግ የተፈጥሮ ማዳበሪያን አዘጋጅቶ መጠቀም ጠቀሜታው የጎላ ነው። ለዚህም በበጀት ዓመቱ ከ3 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚበልጡ አርሶ አደሮችን በተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅት በማሳተፍ 86 ሚሊዮን ሜትር ኩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ግብ ተይዞ ወደተግባር ተገብቷል። ከቅጠላቅጠሎች፣ ከተረፈ ምርት፣ ከከብቶች እዳሪ፣ ከአመድና ለኮምፖስት ዝግጅት ጠቃሚ ከሆኑ ሌሎች ንጥረ ነገሮች ጥራቱን ጠብቆ እንዲዘጋጅ ለአርሶ አደሩ ሙያዊ ድጋፍ እየተሰጠ መሆኑንም ገልጸዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያ ሳይንሳዊ ሂደቱን ጠብቆ ከተዘጋጀ የአፈር ቅንጣትና ለምነት እንዲሻሻል፣ የሰብል ምርታማነት እንዲጨምር፣ አፈር በውስጡ ውሃን ለረጅም ጊዜ እንዲቋጥር የጎላ ጠቀሜታው እንዳለውም አመልክተዋል። በበጀት ዓመቱ የሚዘጋጀው የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለቀጣይ ዓመት መስኖና የመኽር እርሻ ጥቅም ላይ ለማዋል ከወዲሁ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በማዳበሪያ ዝግጅቱ እየተሳተፉ ካሉት መካከል በምዕራብ ጎጃም ዞን ቡሬ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ታደሰ አለሙ በሰጡት አስተያየት የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማዘጋጀትና መጠቀም ከጀመሩ ከ15 ዓመት በላይ እንደሆናቸው ገልጸዋል። በተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘገጃጀት ላይ ከግብርና ባለሙያዎች ባገኙት የካበተ ልምድና ዕውቀት በዓመት እስከ 23 ሜትር ኩብ ኮምፖስት ማዳበሪያ በጥራት አዘጋጅተው እንደሚጠቀሙ ተናግረዋል። የሚያዘጋጁትን ኮምፖስት ማሳቸው ላይ በመጨመር የአፈር ለምነትን ከማሻሻል ባለፈ የሰብል ምርታማነትና ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን አመልክተዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያ አዘጋጅተው መጠቀም ከጀመሩ ወዲህ ለምነቱን አጥቶ ከምርት ውጭ ሆኖ የቆየ ግማሽ ሄክታር መሬት ለምነቱ መመለሱን የገለጹት ደግሞ በዞኑ የሰከላ ወረዳ አርሶ አደር ፈጠነ አስረስ ናቸው። ከዚህም በየዓመቱ እስከ 12 ኩንታል የስንዴና የገብስ ምርት በመሰብሰብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው፣ በተያዘው በጀት ዓመትም 18 ሜትር ኩብ ኮምፖስት በጥራት አዘጋጅተው ለመጠቀም ወደሥራ መግባታቸውን ተናግረዋል። የቢሮው መረጃ እንደሚያመለክተው በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተዘጋጀ ከ81 ሚሊዮን ሜትር ኩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለመስኖና ለመኸር ሰብል ልማት ጥቅም ላይ መዋሉ ታውቋል።