ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ኢትዮጵያ በልማት እንቅስቃሴዎችና በውጭ ግንኙነት መስክ ተጨባጭ ውጤቶችን እያስመዘገበች ትገኛለች
Jul 20, 2026 51
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በልማት እንቅስቃሴዎችና በውጭ ግንኙነት መስክ ያስመዘገበቻቸው ውጤቶች የሀገሪቱን ሁለተናዊ ብልፅግና ከማረጋገጥ ባለፈ የውሳኔ ሉዓላዊነትን በተግባር ያረጋገጡ መሆናቸውን ምሁራን ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማሲና ዓለምአቀፍ ግንኙነት መምህር እንዳለ ንጉሤ እንደገለጹት፤ በፖለቲካ ሳይንስና ዲፕሎማሲ መስክ ሉዓላዊነት ሀገራት በውስጣዊም ሆነ በውጭ ጉዳዮቻቸው ላይ ያለማንም ጣልቃ ገብነት በነፃነት የመወሰን ሙሉ ባለቤትነትን ማረጋገጥ መቻል ነው። ከለውጡ በኋላ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟን ማዕከል ያደረገ የዲፕሎማሲ አካሄድ እየተከተለች እንደምትገኝ ገልፀው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅና ወደ ሥራ ማስገባት የመወሰን ነጻነት የታየበት ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ሕጋዊና ሞራላዊ መሠረት ያለው የባህር በር የማግኘት ጥያቄን በማንሳት ለዓለም ማህበረሰብ የማስገንዘብ ተግባር እያከናወነች መሆኗም የውሳኔ ሉዓላዊነቷ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። በሀገር ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያን ሁለተናዊ ዕድገት ከማረጋገጥ ባለፈ፣ ለአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች መጠናከር ያላቸውን ቁልፍ ሚና በግልጽ ያሳያሉ ብለዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ዶክተር መብራቱ አለሙ በበኩላቸው የዲፕሎማሲ አቅም ከሀገር ውስጥ የኢኮኖሚ ጥንካሬ ጋር የተሳሰረ መሆኑን ገልፀዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት መንግስት ወደ ተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ትግበራ መግባቱ የውጭ ምንዛሬ እጥረት፣ የዕዳ ጫናና የዋጋ ንረት ችግሮችን መፍታት ማስቻሉን አንስተዋል። የግል ዘርፉን በማጠናከር፣ የውጭ ባንኮችና ካፒታል ወደ ሀገር እንዲገቡ በር በመክፈትና የካፒታል ገበያን ስርዓትን በመዘርጋት የሀገሪቱን የፋይናንስ አቅም ማሳደጉን ገልፀዋል። በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚም የኤክስፖርት መጠንን በማሳደግና በብድርና በእርዳታ ላይ ያለውን ጥገኝነት በመቀነስ የውሳኔ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በከተሞች በኮሪደር ልማት እየተመዘገበ ያለው ፈጣን እድገት የሀገሪቱን ዓለምአቀፍ ገጽታና የኮንፍረንስ ቱሪዝም ማዕከልነት እያሳደገ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟን ማዕከል ያደረገ ባለብዙ ዘርፍ ዲፕሎማሲና ለጎረቤት ሀገራት ቅድሚያ የመስጠት መርህን እየተከተለች መሆኗም ለዲፕሎማሲ ስኬቷ መሰረት መሆኑን ምሁራኑ ተናግረዋል።
በኦሮሚያ ክልል በተካሄደ የኦዲት ክትትል ግኝቶች ላይ አስፈላጊው የማስተካከያ እርምጃ እንዲወሰድ ተደርጓል 
Jul 20, 2026 58
አዳማ፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በተካሄደ የኦዲት ክትትል ግኝቶች ላይ አስፈላጊው የማስተካከያ እርምጃ እንዲወሰድ መደረጉን የክልሉ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ኃላፊ አቶ ተፈሪ ወንድይፍራው ተናገሩ። ለሁለት ቀናት የተካሄደው የጨፌ ኦሮሚያ 6ኛ የሥራ ዘመን 5ኛ ዓመት 11ኛ መደበኛ ጉባዔ የክልሉን ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ሪፖርትን እና የዳኞች ሹመትን በማፅደቅ ተጠናቋል።   የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የክልሉ ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤትን ሪፖርት ያቀረቡት ኃላፊው አቶ ተፈሪ ወንድይፍራው፤ የመንግሥት ገቢ እና ወጪ በሕግና መመሪያ መሠረት መሰብሰቡን እና መውጣቱን ለማረጋገጥ ኦዲት መደረጉን ተናግረዋል። በኦዲት ሥራውም በ48 መሥሪያ ቤቶች 195 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ሳይሰበሰብ መገኘቱን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ከ220 ሚሊዮን ብር በላይ ሕግን ሳይጠብቅ የበጀት ዝውውር ሥራ ላይ መዋሉ በተደረገው ኦዲት መገኘቱንም ገልጸዋል። በተከናወነው የኦዲት አፈጻጸም ክትትል በታዩት ግኝቶች ላይ አስፈላጊው የማስተካከያ እርምጃ መወሰዱን ጠቅሰዋል። በ16 መሥሪያ ቤቶች ላይ በተደረገ ክትትልም በኦዲት ሪፖርቱ በተሰጠው የማሻሻያ ሐሳብ መሠረት የተለያዩ እርምጃዎች መወሰዳቸውን ጠቁመዋል። በ2019 በጀት ዓመትም ለብልሹ አሠራር ተጋላጭ በሆኑ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችና የልማት ድርጅቶች ውስጥ ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ የኦዲት አገልግሎት ይጠናከራል ብለዋል። በክልሉ የበጀት፣ የንብረትና የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ በእጥፍ እየጨመረ በመሆኑ የመሥሪያ ቤቱ ባለሙያዎችን አቅምና ብቃት ማሳደግ፣ የንብረት ክትትልና ቁጥጥርን ማጠናከር እንዲሁም የኦዲት ሽፋንን ማሳደግ ላይ በትኩረት እንደሚሠራ ገልጸዋል። በኦሮሚያ ጨፌ የመንግሥት በጀትና የሀብት ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴም የዋናው ኦዲተር መሥሪያ ቤት የተሰጠውን ኃላፊነት በአግባቡ ለመወጣት የተለያዩ የኦዲት ዓይነቶችን ሲያካሂድ መቆየቱን ገልጿል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ገመቹ አራርሳ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤ የመንግሥት አሠራር ባልተከበረባቸው ቦታዎች ላይ በኦዲት ግኝቶች ላይ የተመሠረተ እርምጃ እንዲወሰድ ሲደረግ መቆየቱን ተናግረዋል።
በደብረ ብርሃን ከተማ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ተጠቃሚ አድርገውናል
Jul 20, 2026 73
ደብረብርሃን፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦ በደብረ ብርሃን ከተማ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ዘላቂ ተጠቃሚነታችንን ያረጋገጡ ናቸው ሲሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። ከደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ በለጡ አስፋው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተማዋ የልማት፣ የሰላምና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች በትኩረት መሰራታቸው ተጠቃሚ እንድንሆን አድርጎናል ብለዋል። በተለይም ወንጀል ይፈፀምባቸው የነበሩ አካባቢዎችን በማልማት ውብ፣ ሳቢና ማራኪ የመዝናኛ ስፍራ እንዲሆን መደረጉ በተሻለ መንገድ ነዋሪውን ተጠቃሚ ለማድረግ ያስቻሉ ናቸው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የከተማዋን አድገት በሚያፋጥኑ የልማት ስራዎች ላይ በጉልበት፣ በገንዘባቸው እና በእውቀታቸው በመሳተፍ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ገልጸዋል። ሌላው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ሠይድ ማሩ በበኩላቸው፤ በከተማው የተካሄዱ የመንገድና ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ለወጣቶችና ለሴቶች የሥራ ዕድልን የፈጠሩ ናቸው ብለዋል። የተገነቡ የመሰረተ ልማቶች የአገልግሎት ጊዜያቸው እንዲረዝም የአካባቢውን ማህበረሰብ በማስተባበር የመጠበቅና የመንከባከብ ስራ እየሰሩ መሆኑን ነው ያመለከቱት። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሽት በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተከናወኑ የልማት ስራዎች ከተማዋን የኢንዱስትሪ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ማእከል እንድትሆን ያስቻሉ ናቸው።   በዚሁ ወቅት ሰላምን ከማስጠበቅ ጎን ለጎን ህብረተሰቡ የተሳተፈበት የ75 ኪሎ ሜትር የጠጠርና ሶስት ኪሎ ሜትር የኮብል ስቶን መንገዶች መገንባታቸውን አስረድተዋል። በተለይም በከተማዋ የተገነባው የሶስት ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ ደረጃውን የጠበቀ የእግረኛና የሳይክል መንገዶችን ጨምሮ የመዝናኛ እና የአረንጓዴ ስፍራዎችን ያካተተ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የቴሌኮሙኒኬሽንና የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማቶችን አሟልቶ የተገነባ በመሆኑ ለከተማዋ እድገትና ለህዝቡ ተጠቃሚነት የላቀ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ19 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ እድል መፈጠሩን ጠቁመው በአዲሱ በጀት ዓመትም ከዚህ የላቀ ስራ ለመስራት በቁርጠኝነት እየተንቀሳቀሱ እንደሚገኙ አመልክተዋል።
በአማራ ክልል በ42 የተለያዩ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ ተከናውኗል
Jul 20, 2026 57
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ) ፡-በአማራ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ42 የተለያዩ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ መከናወኑን የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ አስታወቀ። የአማራ ክልል ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ አማካሪ ሽቤ ክንዴ፤ በተለይም በከተሞች ልማት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተከናወኑ አበይት ተግባራትን በተመለከተ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም በክልሉ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራዎችን በማስፋፋት ዘመናዊ በማድረግ ለኑሮ፣ ለኢንቨስትመንትና ለጉብኝት ጭምር ምቹ ማድረግ ስለመቻሉ አንስተዋል። በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ42 የተለያዩ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ ስለመከናወኑ ጠቅሰው በዚህም የዜጎችን ተጠቃሚነት እውን ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የኮሪደር ልማቱ የእግረኛ፣ የተሽከርካሪ፣ የብስክሌት መንገድን ጨምሮ የአረንጓዴ ልማት፣ የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች፣ የመዝናኛ ስፍራዎችና መሰል አገልግሎቶችን አካቶ የተሰራ መሆኑን ጠቅሰው በተያዘው በጀት ዓመትም ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በልማቱ ከ214 ኪሎ ሜትር በላይ የመንገድ ስራ እንዲሁም ከ100 ሄክታር በላይ የተለያዩ አካባቢዎችን በአረንጓዴ ልማት የማስዋብ ስራ ተሰርቷል ብለዋል። በዚህ የልማት ስራ ከ199 ሺህ 700 ለሚበልጡ ወገኖች የስራ እድል ስለመፈጠሩ አንስተው ልማቱ ቀጣይነት ይኖረዋል ብለዋል። የአንድ ከተማ አንድ ፕሮጀክት የልማት እንቅስቃሴም በ205 ከተሞችና ክፍለ ከተሞች 281 ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ሲሆን አብዛኞቹ ተጠናቀው ለህዝብ አገልግሎት እንዲውሉ መደረጉንም አንስተዋል። በቀጣይም ልማቱን ወደ ሌሎች ከተሞች ለማስፋት መታቀዱን ያነሱት አቶ ሽቤ፤ የዜጎች እገዛና ተሳትፎ ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
የገበያ አማራጮችን በማስፋትና ህገ ወጥነትን በመቆጣጠር ለገበያ መረጋጋት የሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jul 20, 2026 53
ኮምቦልቻ ፤ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፡- የገበያ አማራጮችን በማስፋት፣ የምርት አቅርቦትን በማሳለጥና ህገ ወጥነትን በመቆጣጠር ለገበያ መረጋጋት የሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን የአማራ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የተጠናቀቀው በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ግምገማና የአዲሱን በጀት ዓመት እቅድ የትውውቅ መድረክ በኮምቦልቻ ከተማ እያካሄደ ነው።   በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የአማራ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢብራሂም መሐመድ (ዶ/ር)፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በገበያ አቅርቦትና ዋጋን በማረጋጋት ረገድ ብዙ ስኬታማ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም የገበያ አማራጮችን በማስፋት፣ የምርት አቅርቦትን በማሳለጥና ህገ ወጥነትን በመቆጣጠር ለገበያ መረጋጋት የሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።   የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ንግድንና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ዮናስ መላኩ፤ በከተማው የገበያ ማዕከላትን በማስፋፋት የምርት አቅርቦትና ተደራሽነት ላይ በቅንጅት መሰራቱን አንስተው ቀጣይነት የሚኖረው መሆኑን አረጋግጠዋል። በመድረኩ የክልል፣ የዞንና የወረዳዎች በየደረጃው ያሉ የስራ ሃላፊዎችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው።  
ብልጽግና ፓርቲ በተለያዩ ኢኒሼቲቮች በርካታ ስኬቶችን አስመዝግቧል-አቶ አደም ፋራህ
Jul 20, 2026 128
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦ ባለፉት ዓመታት የብልጽግና ፓርቲ የተለያዩ ኢኒሼቲቮችን በመቅረጽ ወደ ተግባር በማስገባት በርካታ ስኬቶችን ማስመዝገቡን የፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ ገለጹ። በአቶ አደም ፋራህ የተመራ የፓርቲው የዋናው ጽህፈት ቤት እና የክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት አመራሮች ቡድን በአዲስ አበባ ከተማ እየተከናወነ ያለውን የተቋማት ግንባታ ስራ ተዘዋውሮ ተመልክቷል። አቶ አደም ፋራህ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በብልጽግና ፓርቲ መሪነት የተከናወኑ የተለያዩ ስራዎች ስኬት አስመዝግበዋል።   የተለያዩ ኢኒሼቲቮችን በመቅረጽ ዘርፈ ብዙ ስራዎች ተከናውነው በርካታ ስኬት መምጣቱን አንስተው፤ የተመዘገበውን ስኬት ይበልጥ አጠናክሮ ማስቀጠል የፓርቲው ቀጣይ ትኩረት መሆኑንም አብራርተዋል። አመራሮቹ ከጉብኝት ባለፈ በመዲናዋ ባሉ የፓርቲው ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች ችግኝ በመትከል አረንጓዴ ዐሻራቸውን አኑረዋል።
በጌዴኦ ዞን ከ44 ሺህ 700 ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ወደ ተግባር ተገብቷል
Jul 20, 2026 85
ዲላ፤ ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን በ2018/19 የመኸር አዝመራ ወቅት ከ44 ሺህ 700 ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ትግበራ መገባቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለጸ። በመኸር አዝመራው ከሚለማው መሬት ከ7 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱም ተመልክቷል።   በዞኑ የመኸር አዝመራ ንቅናቄ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ በመኸር እርሻ ወቅት ሊለማ የሚችልን መሬት ወደ ልማት በማስገባት የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ ይሠራል ብለዋል። በተለይም መሬትን ደጋግሞ በማረስና የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሻሻል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት ተሠርቷል ነው ያሉት። ዞኑ ከቡናና ከሌሎች ቋሚ ሰብሎች ጎን ለጎን በተያዘው መኸር ፈጥነው የሚደርሱና የምግብ ዋስትና ክፍተትን የሚሸፍኑ ሰብሎችም እንደሚለሙ ገልጸዋል። ለዚህም ምርጥ ዘርና ማዳበሪያን ጨምሮ የግብዓት ስርጭት በወቅቱ እንዲከናወን ከማድረግ ባለፈ አርሶ አደሩ በኩታ ገጠም እንዲያለማም የቅርብ ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል። የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ተገኝ ታደሰ በበኩላቸው፣ በመኸር አዝመራው 44 ሺህ 715 ሄክታር መሬት በሰብል ለማልማት ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል።   ከዚህ ውስጥም 26 ሺህ 158 ሄክታር መሬት በአዝዕርት፣ አትክልትና ስራስር ሰብሎች የሚለማ ሲሆን በተለይ ገብስ፣ ጤፍ፣ ስንዴ፣ አተር፣ ባቄላና ድንች ዋና ዋናዎቹ ናቸው ብለዋል። የተቀረው በእንሰትና ፍራፍሬ የሚሸፈን መሆኑን አንስተው በአጠቃላይ ከተያዘው የመኸር አዝመራ ከ7 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱን ተናግረዋል። እቅዱን ለማሳካት የማሳ ዝግጅትና የግብዓት ስርጭት መከናወኑን አንስተው በየደረጃው የሚገኝ የግብርና አመራርና ባለሙያ በቅንጅት እየሠሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በንቅናቄ መድረኩ የዞንና የሁሉም ወረዳዎች አስተዳዳሪዎች፣ የዘርፉ የሥራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።  
በድሬደዋ ከ71 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወሰዱ
Jul 20, 2026 103
ድሬደዋ፣ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦በድሬደዋ አስተዳደር በበጀት አመቱ ከ71 ቢሊዮን ብር በላይ ያስመዘገቡ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መውሰዳቸውን የአስተዳደሩ ኢንቨስትመንት ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የኢንቨስትመንት ፕሮጀክት ጥናት፣ መረጃ ዝግጅትና ፕሮሞሽን ቡድን አስተባባሪ አቶ አበራ መንግስቱ ዛሬ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ አስተዳደሩ ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት በቀየሰው ምቹ ሁኔታ በበጀት አመቱ ከ71 ቢሊዮን 304 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ 464 ባለሃብቶች ፈቃድ ወስደዋል። በአምራች ኢንዱስትሪ፣በአገልግሎት፣በኮንስትራክሽንና በግብርና ዘርፎች ፈቃድ የወሰዱት አልሚዎችም ሙሉ በሙሉ ወደ ስራ ሲገቡ ከ21 ሺህ 650 በላይ ቋሚና ጊዜያዊ የስራ ዕድል ይፈጥራሉ ብለዋል። አስተዳደሩ አልሚዎቹን ውጤታማ ለማድረግ መሠረተ ልማቶችን ከማሟላት ባሻገር ክትትልና ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በአስተዳደሩ የተተገበረው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ፣የተቀናጀ ድጋፍ እና ክትትል የኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት በማሳደግ ተኪ ምርቶችን ማሳደግና የውጭ ምንዛሬን ማስፋት መቻሉን ጠቅሰዋል።   በዚህም በርካታ ኢንዱስትሪዎችም ከመካከለኛ ወደ ከፍተኛ ደረጃ ማደግ እንደቻሉና ለዜጎችም የስራ ዕድል እንዲፈጥሩ ማገዙን ገልጸዋል። ይህም ድሬደዋን በኢንቨስትመንት ዘርፍ የምስራቅ ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ማዕከልነቷን ከማሳደግ በላይ የአስተዳደሩን ማህበራዊ እና ምጣኔ ሃብታዊ እንቅስቃሴዎች በከፍተኛ ደረጃ ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። በኢንቨስትመንት ዘርፉ ፈቃድ ወስደው እንቅስቃሴ ለጀመሩ ባለሃብቶች ከአስተዳደሩ መሬት ልማትና ማኔጅመንት ቢሮ ጋር በመቀናጀት ከ50 ሄክታር መሬት በላይ መቅረቡን አቶ አበራ ጠቁመዋል። ኢንቨስትመንቱን ለማስፋትም የመስሪያ ማሽኖችን ከታክስ ነፃ እንዲያስገቡ መደረጉንና የፋይናንስ፣የውሃ፣ የመንገድና የኤሌክትሪክ አገልግሎቶች እንዲሟሉ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በትብብር መሰራቱን አንስተዋል። በሆቴልና በቡና ማቀናበር ዘርፍ ፍቃድ ከወሰዱ ባለሃብቶች መካከል አቶ ተካልኝ አበበ እና አቶ አብዱልጀባር አሊ በበኩላቸው፥ አስተዳደሩ ለባለሃብቶች እየፈጠረ የሚገኘው ምቹ የስራ አካባቢና የሚያደርገው ድጋፍ አስደሳች መሆኑን ገልጸዋል።  
የሕዳሴ ግድብ የዘመናት ኢ-ፍትሐዊነትን የሻረ የጋራ ተጠቃሚነት ተምሳሌት ነው
Jul 20, 2026 155
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በዓባይ ወንዝ ላይ ነበረውን የዘመናት ኢ-ፍትሐዊ የውሃ ሃብት አጠቃቀም ያስወገደ፣ አዲስ የትብብር እና የጋራ ተጠቃሚነት ተምሳሌት መሆኑን የሕዝብ ተወካች ምክር ቤት አባል መሐመድ አል-አሩሲ ገለጹ፡፡ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ኢትዮጵያውያን የታሪክ ቁጭታቸውን በተግባር ለመቀየር የቆረጡበትና በማንኛውም ውጫዊ አካል ሳይሆን በራሳቸው የውስጥ አቅምና በሕዝብ ሁለንተናዊ አስተዋጽኦ ብቻ የተገነባ ታሪካዊ ፕሮጀክት ነው። ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት አገሪቱ ካላት የተፈጥሮ ሀብት ተጠቃሚ ለመሆን የምታደርገውን ጥረት የሚያሳይ ከመሆኑም በላይ፣ በታዳሽ ኃይል ልማት ረገድ የኢኮኖሚና የቴክኖሎጂ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የጀመረችውን ስልታዊ ጉዞ በግልጽ ያሳያል። ይህ የኢትዮጵያውያን የመቻል አቅም ማረጋገጫ የሆነው ሜጋ ፕሮጀክት፣ የአፍሪካ አገራት የራሳቸውን የውስጥ አቅም አስተባብረው ከተንቀሳቀሱ ያለምንም ውጭ ድጋፍ ትልልቅ የልማት ግቦችን ማሳካት እንደሚችሉ ትልቅ ማሳያ ሆኗል። በመሆኑም ግድቡ ለአፍሪካ አህጉር ነፃነትና ራስን የመቻል አዲስ ተስፋን በማስረፅ ረገድ ታላቅ ኩራትና የማይደበዝዝ የታሪክ ትምህርት የሰጠ ሆኖ ተመዝግቧል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል መሐመድ አል-አሩሲ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ግብፅ በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዙሪያ የምታነሳቸው ነጥቦች ታሪካዊ እውነታዎችን፣ የላይኛው ተፋሰስ አገራትን የልማት መብት እንዲሁም ዓለም አቀፍ የውሃ አስተዳደር ሕጎችን የሚጋፉ መሆናቸውን አስረድተዋል። ይህ የግብፅ አካሄድ ጊዜ ያለፈበትን የውሃ የበላይነት ዘመን እንደገና ለማንፀባረቅ የሚደረግ ዋጋ ቢስ ሙከራ መሆኑንም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የምታከናውናቸው ተግባራት በሙሉ ዓለም አቀፋዊ መርሆዎችን የተከተሉ መሆናቸውን የምክር ቤት አባሉ አብራርተዋል። ዓለም አቀፍ ሕግ የላይኛው ተፋሰስ አገራትን ያገለለ እና በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈረሙ ስምምነቶችን እንደማይቀበል የገለጹት አቶ መሐመድ፣ ኢትዮጵያ፣ ግብፅ እና ሱዳን በ2015 ዓ.ም በካርቱም የፈረሙትን የመርሆች መግለጫ በማስታወስ ግድቡን የመሙላት ሂደት ከዚህ ስምምነት ጋር በሚጣጣም መልኩ መከናወኑን አስረድተዋል። ኢትዮጵያ በዓባይ ወንዝ የገነባችው ታላቁ የህዳሴ ግድብ የቀደመውን ኢ-ፍትሃዊ አሰራር በመቀየር፣ መላውን የናይል ተፋሰስ ይበልጥ ፍትሃዊ፣ ምክንያታዊ እና ሁሉን አቀፍ በሆነ መንገድ ለመምራት የሚያስችል ታሪካዊ ሽግግር መፍጠሩንም ገልጸዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያውያን የውስጥ አቅምና ሀብት የተከናወነ መሆኑን ነው ያስታወሱት መሐመድ አል-አሩሲ፣ ፕሮጀክቱ የሕዝቡን የልማትና የእድገት ፍላጎት በግልጽ የሚያሳይ የታሪክ አሻራ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህም ኢትዮጵያ ግድብ መገንባት ብቻ ሳይሆን፣ በናይል ተፋሰስ ቀጠና ውስጥ አዲስ የፍትህ እና የእኩልነት ታሪክ ጽፋለች ብለዋል። ግብፅ የድርድር ሂደቱን በተደጋጋሚ በማዘግየትና ከግድቡ ቴክኒካዊ ወሰን ውጭ የሆኑ ሰፊ የውሃ ክፍፍል አጀንዳዎችን በማንሳት የፕሮጀክቱን ጉዞ ለማደናቀፍ ስትሞክር መቆየቷን የፓርላማ አባሉ አስታውሰዋል።
በድሬዳዋ ባለፉት ዓመታት የተመዘገቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስኬቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Jul 19, 2026 255
ድሬዳዋ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ ባለፉት አምስት ዓመታት በልማትና በመልካም አስተዳደር የተመዘገቡ ስኬቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የመንግስት ዋና ተጠሪ ኢብራሒም ዩሱፍ ገለጹ። የአስተዳደሩ ምክርቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ኢብራሒም ዩሱፍ ዛሬ በሰጡት መግለጫ እንደገለጹት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። በተለይ የገጠርና የከተማ ነዋሪዎችን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በተቀናጀ መንገድ ለመፍታት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን አንስተዋል። የድሬዳዋን የንግድ፣ የኢንዱስትሪ እና የአገልግሎት ማዕከልነት በተጨባጭ ያረጋገጡ አዳዲስ አምራች ኢንዱስትሪዎች እንዲሁም ደረጃቸውን የጠበቁ ዘመናዊ ሆቴሎችና የሎጅስቲክ ማሳለጫ ማዕከላት ተገንብተው ለአገልግሎት መብቃታቸውን አስረድተዋል። በተለይ በመጀመሪያው ምዕራፍ በከተማዋ ዋና ዋና አካባቢዎች ከ16 ኪሎ ሜትር በላይ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ድሬዳዋን ጽዱ፣ ውብና ለኑሮ ተመራጭ እያደረጋት መምጣቱን ገልጸዋል። ታሪካዊ ቅርሶችን በጠበቀና ገጽታዋን በሚገነባ መልኩ የተከናወነው የኮሪደር ልማት በከተማዋ አዳዲስ መሠረተ ልማቶች እንዲስፋፉ ማድረጉንም ጠቁመዋል። መሰረተ ልማቶቹ ባለሀብቶችን ከመሳብ በተጨማሪ የትራፊክ መጨናነቅን በማስቀረት የተሽከርካሪ አደጋን ለመቀነስ አስችለዋል ብለዋል። በመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የፌደራልና የአስተዳደሩ ተቋማት ተቀናጅተው ፈጣንና ቀልጣፋ ዲጂታል አገልግሎት በመስጠታቸው የዘመናት የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን እየፈታ መሆኑንም አቶ ኢብራሒም ተናግረዋል። እንደ እሳቸው ገለጻ በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን ለሕብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ የኑሮ ውድነትን ማቅለል የሚያስችል ውጤታማ ሥራ ተከናውኗል። በአስተዳደሩ አገልግሎት መስጠትና ማምረት በጀመሩ ተቋማትና ኢንዱስትሪዎች በብዙ ሺህ ለሚገመቱ ወጣቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉንም የመንግስት ዋና ተጠሪው አንስተዋል። በኢንተርፕራይዝ የተደራጁ ወጣቶችን ውጤታማ ለማድረግ የስልጠና፣ የመስሪያ ቦታ፣ የብድርና የሙያ ድጋፍ መሰጠቱንም አመልክተዋል። ባለፉት 5 ዓመታት በሁሉም ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤቶችን በላቀ ደረጃ ለማሳደግ አስተዳደሩ የተቀናጀ እንቅስቃሴ መጀመሩንም አቶ ኢብራሒም ተናግረዋል።
ጨፌ ኦሮሚያ ለክልሉ መንግሥት የ2019 በጀት ዓመት ሥራ ማስፈጸሚያ 704 ቢሊዮን ብር በጀት አጸደቀ
Jul 19, 2026 227
አዳማ፣ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ጨፌ ኦሮሚያ ለተያዘው በጀት ዓመት ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ዕቅድ ማስፈጸሚያ የሚውል 704 ቢሊዮን ብር በጀት በሙሉ ድምፅ አጸደቀ። ጨፌ ኦሮሚያ በ6ኛ የሥራ ዘመን 5ኛ ዓመት 11ኛ መደበኛ ጉባኤው የዛሬ ውሎ የክልሉን መንግሥት የ2019 በጀት አጽድቋል። የኦሮሚያ ክልል ገንዘብ ቢሮ ኃላፊ አቶ ቶሎሳ ገደፋ የበጀት ዝርዝሩን ለጨፌው ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት፤ በጀቱ ከተረጂነት ለመውጣትና ራስን ለመቻል የተያዘውን ግብና ስትራቴጂ ለማሳካት ያለመ ነው። የበጀት ድልድሉም የልማት ፕሮግራሞችን መሠረት በማድረግና የክልሉን ዕድገት ለማፋጠን በሚያስችል መልኩ ተከናውኗል ብለዋል። የልማት ዕቅዱን ውጤታማ ለማድረግ ከሁሉም የክልሉ ሴክተር ተቋማት ጋር ውይይት መደረጉን የጠቀሱት ኃላፊው፤ ትኩረት ለሚሹ ጉዳዮች በበጀት ድልድሉ ቅድሚያ መሰጠቱን ተናግረዋል።   በጀቱ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ76 በመቶ ጭማሪ ያለው ሲሆን፣ የበጀት ድልድሉ የልማት ፕሮጀክቶችን ታሳቢ ባደረገ መልኩ በተለይም በከተሞችና በወረዳዎች ለሚከናወኑ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቷል ብለዋል። በዚህም መሠረት ለጤና፣ ለትምህርት እና ለመንገድ መሠረተ ልማት አንዲሁም ለመስኖ እና ለንጹሕ መጠጥ ውኃ አቅርቦት ቅድሚያ ተሰጥቷል ነው ያሉት። ይህ በጀት በከተሞችና በወረዳዎች መካከል ሊኖር የሚችለውን የመሠረተ ልማት ልዩነት ለማጥበብና በክልሉ ቆላማ አካባቢዎች የሚገኙ ሰፋፊ መሬቶችን ለማልማት የሚያስችሉ የመስኖ ፕሮጀክቶችን ለማከናወን ታሳቢ ማድረጉንም ኃላፊው ገልጸዋል። ከተሞችና ወረዳዎች የሚሰጣቸውን በጀት ለማኅበራዊ መሠረተ ልማት ማዋል ላይ ትኩረት አድርገው መደልደል እንዳለባቸውም አሳስበዋል። ማንኛውንም የገቢ ዓይነት ያለ ሕጋዊ ደረሰኝ መሰብሰብ የተከለከለና የሕግ ተጠያቂነት የሚያስከትል መሆኑንም አሳስበዋል። የጨፌው አባላት በቀረበው የበጀት ቀመር ላይ በሰጡት አስተያየት፤ የበጀት ድልድሉ ከተረጂነት ለመውጣትና ራስን ለመቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። ሆኖም ከበጀት ድልድሉ ባለፈ፣ የካፒታል በጀትን ጨምሮ የተመደበው ሀብት ለታለመለት ዓላማ ብቻ እንዲውል ጠንካራ ድጋፍና ክትትል ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ በዋና ዋና የልማት ዘርፎች ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ተመዝግበዋል
Jul 19, 2026 133
አዳማ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ በዋና ዋና የልማት ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤቶች መመዝገባቸው ተገለጸ። እየተካሄደ ባለው የጨፌ ኦሮሚያ 11ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ የጨፌው አባላት የሰላም ማስፈንና የመሰረተ ልማት ዝርጋታ ሥራዎችን የተመለከቱ ጥያቄዎችን አንስተዋል። ለተነሱት ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ የሰጡት የክልሉ መንግስት የተለያዩ ዘርፎች የሥራ መሪዎች በበጀት ዓመቱ ተስፋ ሰጪ ስራዎች መከናወናቸውን አንስተዋል። የኦሮሚያ ክልል የአስተዳደርና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ፤ የክልሉን ሰላም ለማረጋገጥ በተከናወነው የተቀናጀ ሥራ የክልሉ ሰላም እየተሻሻለ መጥቷል ብለዋል።   ህብረተሰቡ እና መንግስት በጋራ በሰሩት ሥራ የክልሉ ሰላም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ መምጣቱን ጠቅሰው፣ ለዚህም በክልሉ 7ኛው ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ ሆኖ መጠናቀቁ አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል። መንግስት የክልሉን የጸጥታ አካላት አቅም ለማጠናከር ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ሲሆን፣ ይህንን ለማሳካትም አቅም የመገንባትና የማብቃት ሥራዎች ላይ ትኩረት ተደርጎ እየተሠራ መሆኑን አመልክተዋል። አሁንም በክልሉ ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ አካላት የቀረበላቸውን የሰላም ጥሪ የሚቀበሉ ከሆነ የክልሉ መንግስት ለመነጋገር ዝግጁ ሆኖ እየጠበቀ ይገኛል ሲሉም ገልጸዋል። በሌላ በኩል የኦሮሚያ ክልል መንግሥት የትምህርት ጥራትን በማረጋገጥ ተወዳዳሪ ትውልድ ለማፍራት የጀመረው ሥራ ስኬታማ እየሆነ መምጣቱን የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ቶላ ባሪሶ ገልጸዋል።   በክልሉ የትምህርት ሥራ በጥሩ ሂደት ላይ መሆኑን ያነሱት ኃላፊው፣ ተማሪዎች በሥነ-ምግባር ታንጸውና ብቁ ዜጋ ሆነው እንዲወጡ የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል ብለዋል። በተመሳሳይ በክልሉ የአርብቶ አደሩን ሕይወት ለመለወጥ በተከናወነው ሥራ አበረታች ውጤቶች መገኘታቸውን የክልሉ መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ግርማ ረጋሳ ተናግረዋል።   ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ ሥራዎች 512 የመስኖ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ወደ ሥራ ማስገባት መቻሉን ገልጸዋል። የክልሉ መንገዶችና ሎጂስቲክስ ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ሄለን ታምሩ በበኩላቸው የሕዝቡ የመንገድ መሰረተ ልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ እየተመለሱ መሆኑን ተናግረዋል።   በተለይም የኮንትራክተሮች አቅም ማነስ፣ የኮንስትራክሽን ዕቃዎች ዋጋ ንረትና በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ የሚታየው የጸጥታ ችግር ለመንገድ ፕሮጀክቶች መጓተት ምክንያት እንደሆኑ ጠቅሰው፣ እነዚህን ችግሮች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመፍታት የመንገድ ስራዎችን ለማፈጠን ይሰራል ብለዋል። የክልሉን የመጠጥ ውሃ ተደራሽነት ለማሳደግ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶ በተሰራው ስራ የክልሉን የንጹህ መጠጥ ውኃ ሽፋን ማሳደግ መቻሉን የተናገሩት ደግሞ የክልሉ ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ሚሊዮን በቀለ ናቸው።   ቢሮው ከመንግስት በጀት በተጨማሪ የማኅበረሰቡን እና የአጋር አካላትን ተሳትፎ በመጠቀም የመጠጥ ውሃ ሽፋንን ለማሳደግ ተጨባጭ ሥራ ሰርቷል ብለዋል።
የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ የልማት ስኬቶች ስምን ከግብር በማሰናሰል የተገኙ ውጤቶች ናቸው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 19, 2026 151
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ሁለንተናዊ የልማት ስኬቶች ስምን ከግብር በማሰናሰል የተገኙ ውጤቶች መሆናቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ላለፉት ሶስት ተከታታይ ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን የ2018 በጀት ዓመት እና የአምስት ዓመት ስትራቴጂካዊ ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ በስኬት አጠናቋል።   የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ የከተማ አስተዳደሩ በ2018 በጀት ዓመት ከ96 በመቶ በላይ የአፈጻጸም ውጤት አስመዝግቧል። በመዲናዋ በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊ፣ በፖለቲካዊ እና በሌሎች ዘርፎች የተመዘገቡት ስኬቶች ከተማዋን ውብና ጽዱ ከማድረጋቸውም በላይ ዓለም አቀፍ እውቅና ጭምር እንዳስገኙ ገልጸዋል። የኑሮ ውድነትን በማረጋጋት፣ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን በማሳካት፣ እንዲሁም ግልጽነትና ተጠያቂነትን በማስፈን የዜጎችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ መቻሉንም አስታውቀዋል። የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ በበኩላቸው፤ ባለፉት አምስት ዓመታት መዲናዋን ማራኪ ገጽታ በማላበስ ረገድ ሁለንተናዊ ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። የተገኙት ውጤቶችም የሕዝብን ጥያቄዎች ምላሽ በማስገኘት እና ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት በመፈጸም ረገድ የታየው የአመራር ቁርጠኝነት ውጤት መሆናቸውን አስረድተዋል። በቀጣይም የተገኙ ስኬቶችን በማስቀጠልና ክፍተቶችን በማረም የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሥራዎች እንደሚከናወኑ አረጋግጠዋል። በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ በበኩላቸው፤ በ2018 በጀት ዓመት የከተማዋን እና የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና የሚያፋጥኑ ሥራዎች መሠራታቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም የመዲናዋን በጎ ገጽታ በማጎልበት እና የሕዝቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ተጨባጭ ውጤቶችን ማምጣት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ሚሊዮን ማቴዎስ፤ በመዲናዋ የሚከናወኑ ቁልፍ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል እየፈጠሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። የኢንዱስትሪ፣ የከተማ ግብርና፣ የኮንስትራክሽንና የአገልግሎት ዘርፎች የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ያላቸው ፋይዳ ከፍተኛ እንደሆነም አክለዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጀማሉ ጀምበር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የዲጂታል መንግሥት አገልግሎት የተገልጋዮችን እርካታ እያሳደገ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም በአንድ ማዕከል አገልግሎት የተጀመረውን የዘመናዊ አሠራር አቅም ይበልጥ በማጠናከር ተደራሽነቱን እንደሚያሰፉ አስረድተዋል።  
የግብር አሰባሰብ አቅምን በማሳደግ የከተሞችን የመሰረተ ልማት ተደራሽነት በራስ አቅም ለማሳካት ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 19, 2026 119
ቡታጅራ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የከተሞችን የግብር አሰባሰብ አቅም በማሳደግ የመሰረተ ልማት ተደራሽነትን በራስ አቅም ለማሳካት በቅንጅት እንደሚሰራ ተገለጸ። በክልሉ የከተሞቹን እንቅስቃሴ በማሳለጥና ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን በማሳደግ ገቢያቸውን ከማሳደግ ባለፈ የማህበረሰቡን የልማት ጥያቄ በራሳቸው መፍታት እንዲችሉ ለቅንጅታዊ ሥራ ትኩረት ተሰጥቷል። በተያዘው የ2019 በጀት ዓመትም ይህን ተግባር ለማስቀጠል አሳታፊ እቅዶችን በማውጣት ወደስራ መገባቱ ተመላክቷል። ኢዜአ ያነጋገራችው የሆሳዕና፣ ቡታጅራ እና ወልቂጤ ከተሞች ገቢ ጽህፈት ቤቶች የሥራ ሃላፊዎች እንዳሉት በተያዘው የ2019 በጀት ዓመት ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ ልማትን ለማፋጠን አቅደው ወደ ተግባር ገብተዋል። በዚህም ለማህበረሰቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ተገቢ ምላሽ ለመስጠት ለቅንጅታዊ አሰራርና ግብር ስወራን ለመቆጣጠር ትኩረት መስጠታቸውን ተናግረዋል። የሆሳዕና ከተማ ገቢዎች ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አውላቸው ዮሐንስ እንደገለጹት ፤ በከተማው በበጀት ዓመቱ 4 ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል። ገቢውን ከመደበኛና ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ለመሰብሰብ መታቀዱን ገልጸው በእዚህም ለማህበረሰቡ የልማት ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት በቅንጅት ይሰራል ብለዋል። ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች እና በደረሰኝ የሚሰበሰበው ገቢ ላይ የሚስተዋሉ ውስንነቶችን በማረም ገቢን አሟጦ በመሰብሰብ ለአካባቢው ፈጣን እድገት በትኩረት እንደሚሰራም አመልክተዋል። የቡታጅራ ከተማ ገቢዎች ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ወልዩ ከበደ በበኩላቸው እንዳሉት፤ ከተማው የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ በመሰብሰብ የልማት ሥራዎችን በራስ አቅም ለመሸፈን ግብ ተይዞ ወደ ተግባር ተገብቷል። በተያዘው የ2019 በጀት ዓመት በከተማው ከ1 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ መታቀዱንም አመልክተው፣ በተለይም በአገልግሎት ዘርፍ የሚገኝን ገቢ በማሳደግ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ይሰራል ብለዋል። ገቢን በማሳደግ ህዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት ሥራዎችን ለማከናወን ግንዛቤ ከመፍጠር ጀምሮ የታክስ ህግ የማስከበር ሥራ በቅንጅት እንደሚሰራ የተናገሩት ደግሞ የወልቂጤ ከተማ ገቢዎች ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ይድረሱ ተስፋዬ ናቸው። እንደሃላፊው ገለጻ በበጀት ዓመቱ በከተማው 1 ቢሊዮን 77 ሚሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። የግብር አሰባሰብ ሥርአቱን ከማዘመን ባለፈ የግብር ከፋዩን ለግዢ ደረሰኝ የመስጠት ባህልን ለማሳደግና ለህግ ተገዢ እንዲሆን የማድረግ ሥራ ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ መሆኑንም አመልክተዋል።
ዜጎችን ሁሉን አቀፍ በሆነ መልኩ ተጠቃሚ የማድረግ ውጤታማ ስራዎች ተከናውነዋል- ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 19, 2026 145
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በመዲናዋ ዜጎችን ሁሉን አቀፍ በሆነ መልኩ ተጠቃሚ በማድረግ ረገድ ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸውን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። በምናብ ያየነውን አቅደን ተግተን ፈፅመናል፤ 96 በመቶ በላይ ውጤት ማስመዝገብ ችለናል ብለዋል ከንቲባዋ በመልዕክታቸው። ባለፉት ሶስት ተከታታይ ቀናት ሲካሄድ የነበረው የ2018 በጀት ዓመት እና የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ እቅድ አፈፃፀም ግምገማ በስኬት መጠናቀቁን አመልክተዋል።   በግምገማው የታቀዱ ስትራቴጂክ ግቦች በተሟላ ሁኔታ ለመተግበር በተለወጠ የስራ ባህል ያለ ማቋረጥ ቀንና ማታ በመስራት በትጋት የተመዘገቡ ውጤቶችን ማላቅ እና የተለዩ ድክመቶችን በማረም በቀጣይ የተሻለ አፈፃፀም ለማስመዝገብ መግባባት ላይ መደረሱን አመልክተዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት የአገልግሎት አሰጣጡን ዲጂታላይዝ በማድረግ በተለይም ደግሞ በተያዘው በጀት ዓመት ተግባራዊ በተደረገው በመሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል የመንግስት አገልግሎት መቀየሩን ነው ያብራሩት። ማህበራዊ ፍትህን ለማንገስ ማንንም ያልዘነጋ ህፃናት ፥ ተማሪዎች ፥ ሴቶች፥ ወጣቶች ፥ አረጋውያን ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሰው ተኮር ልማቶች በትጋት መሰራቱን ነው ያመለከቱት። 2.2 ሚሊዮን የስራ ዕድል የተፈጠረበት፥ የልማቱ የጀርባ አጥንት የሆነውን የገቢ አሰባሰብ ስርዓት እጅግ ውጤታማ የነበረበት፥ ከ60 ሺህ በላይ ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት በተፈጸመበት፤ ከተማችን ለነዋሪዎቿ ምቹ ፣ ሀገራዊና አህጉራዊ ብሎም ዓለም አቀፋዊ ሚናዋን በብቃት የምትወጣ ፤ አዲስ አበባ ስሟና ግብሯ የተናበበ ፅዱ ፥ አረንጓዴና ውብ ከተማ የማድረግ፤ በአፍሪካ ብቻም ሳይሆን በዓለም መድረክ ጎልታ እንድትታይ አልቀን ፈፅመናል ሲሉም ገልጸዋል።   ከስኬቶቻችን ባሻገር ዛሬም ያልተሻገርናቸው ተግዳሮቶች የአመራራችን የውጤታማነት ልዩነቶች፣ የስነምግባር መጓደል፣ የመረጃ አያያዝ ክፍተቶችን ለማረም ይሰራል ብለዋል። እንዲሁም በቀጣይ የኑሮ ውድነት እና የገበያ ማዛባትን ማስተካከል፥ የስራ እድልን ማስፋት፥ ፅዳትን ባህል ማድረግ፥ አገልግሎትን ማዘመን ፣ የመሶብ ዲጅታል አንድ ማዕከልን ማጠናከር፣ የቤት፥ ትራንስፖርት፥ መንገድ፥ ውሃ አቅርቦት ማሻሻል፥ የከተማ ማደስ በአጠቃላይ የጀመርነውን ልማት በጥራት፣ በስፋትና በፍጥነት ተጠናክሮ ይሰራል ነው ያሉት። ጠንካራ መንግስት የመመስረት ስራም ልዩ ትኩረት የሚሰጠው እና የመረጠንን ህዝብ ይበልጥ በቅንነት ፣ በታማኝነትና በትጋት የምናገለግል መሆኑን ልናረጋግጥላችሁ እንወዳለን ብለዋል ከንቲባዋ በመልዕክታቸው፡፡
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ሕግን ከፍትሐዊ ተጠቃሚነት ጋር ያጣመረ ምክንያታዊ ጥያቄ ነው
Jul 19, 2026 141
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ታሪክን ከመልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ፣ ሕግን ከፍትሐዊ ተጠቃሚነት ጋር ያጣመረ ምክንያታዊ ጥያቄ መሆኑን ሊቢያዊው ምሁር ፕሮፌሰር ሳዕድ ሰላማ ገለጹ። በኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ለመታደም አዲስ አበባ የሚገኙት ሊቢያዊው ፕሮፌሰር ሳዕድ ሰላማ፤ የባሕር በር አልባ ሀገራት የባሕር ተደራሽነት በሌሎች ሀገራት በጎ ፈቃድ ብቻ ሊወሰን አይገባም ብለዋል። ፕሮፌሰር ሳዕድ ለፐልስ ኦፍ አፍሪካ (POA) እንዳሉት፤ የባሕር በር ባለቤትነት በዘላቂ ልማትና የንግድ ትስስር የተመሠረተ መሆኑን በቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሕግጋት በግልጽ ተደንግጓል። የባሕር በር አልባ ሀገራት ወደ ባሕር የመድረስ መብት በዓለም አቀፍ ሕግና ስምምነቶች የተረጋገጠ መሆኑን አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ያላት ሀገር እንደመሆኗ፣ ከሶስት አስርት ዓመታት በፊት የራሷ የባሕር በር እንደነበራት አስታውሰዋል። የሀገሪቱ የረጅም ዘመናት የሥልጣኔ ታሪክም በቀይ ባሕር ቀጣና ከነበራት የወደብ ባለቤትነት ጋር በእጅጉ የተቆራኘ ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ታሪክን ከመልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ፣ ሕግን ደግሞ ከፍትሐዊ ተጠቃሚነት ጋር አጣምሮ የያዘ ምክንያታዊ መሠረት ያለው ጉዳይ መሆኑን ገልጸዋል። ሀገሪቱ ለዚህ መብቷ ምላሽ ለማግኘት የምታደርገው ሰላማዊ የዲፕሎማሲ ጥረት በዓለም አቀፍ ስምምነቶች የተረጋገጠ መሠረታዊ መብት መሆኑን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ በጎረቤት ሀገራት ዘንድ በችሮታና ስጦታ የሚታይ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ሕግጋት የተመሰረተ የተፈጥሮ ሃብትን በትብብርና በጋራ የመጠቀም መብት መሆኑን አስምረውበታል። ይህ ጥያቄ በጋራ ተጠቃሚነት መርህ ላይ ተመሥርቶ ምላሽ ካገኘም የአፍሪካ ቀንድን ሰላም፣ ንግድና የኢንቨስትመንት ትስስር በማጎልበት ከፍተኛ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል። የባሕር በር ባለቤትነት ሰላማዊና በሰጥቶ መቀበል መርህ ላይ የተመሠረተው ዲፕሎማሲያዊ ጥያቄና ጥረት ለቀጣናዊ ትብብርና ዕድገት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። በአዲስ አበባ ቆይታቸው የኢትዮጵያን ዋናው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ሂደትን በመታዘብ ለሀገራቸው ሊቢያ ተጨባጭ ሁኔታ የሚጠቅሙ ልምዶችን እንደሚቀስሙ ገልጸዋል።
በክልሉ በበጀት ዓመቱ ውጤታማ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል 
Jul 19, 2026 96
አዳማ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ ሰላምና መልካም አስተዳደርን ከማረጋገጥ ጎን ለጎን ውጤታማ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውን የክልሉ ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ ተናገሩ። የጨፌ ኦሮሚያ 6ኛ የሥራ ዘመን 5ኛ ዓመት 11ኛ መደበኛ ጉባኤ በአዳማ ገልማ ጨፌ እየተካሄደ ይገኛል።   ፕሬዚዳንቱ የክልሉን መንግሥት የዕቅድ አፈጻጸም ባቀረቡበት ወቅት፣ በበጀት ዓመቱ ሰላምን ከማጽናትና መልካም አስተዳደርን ከማስፈን ጎን ለጎን ለልማት ልዩ ትኩረት በመስጠት በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። በዚህም መሠረት በ2018 ዓ.ም በግብርና፣ በኢንዱስትሪና በአገልግሎት ዘርፎች ውጤታማ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቁመዋል። ግብርና የኢኮኖሚ ዕድገት ዋና ምሰሶ በመሆኑ እየተከናወነ ባለው ሥራ ትላልቅ ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፣ ይህም ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር እየተደረገ ባለው ጥረት ትልቅ እገዛ እያደረገ መሆኑን አመልክተዋል። በ2017/18 የምርት ዘመን በነበረው የመኸር ግብርና ሥራ 11 ነጥብ 8 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቶ የተሻለ ምርት ማግኘት ተችሏል ብለዋል። በ2018/19 የምርት ዘመን የመኸር ግብርና ልማት 12 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ ሰብሎች ይለማሉ ብለዋል። እስከ አሁን ባለው ሂደትም 9 ነጥብ 7 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ታርሶ ለዘር የተዘጋጀ ሲሆን፣ 5 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር የሚሆነው ደግሞ በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ተሸፍኗል ብለዋል፡፡ በተመሳሳይ ከሻይ ቅጠል ልማት ጋር ተያይዞ ከዚህ ቀደም የተተከሉትን ከመንከባከብ ባለፈ፣ ዘንድሮ ልማቱን ለማጠናከር በተደረገ ጥረት እስካሁን ድረስ 17 ነጥብ 9 ሚሊዮን ችግኝ መተከሉን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም ሥራው ቀጣይነት ባለው መልኩ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራም በተጠናቀቀው በጀት ዓመትም እርከኖች፣ የውሃ ማስተላለፊያ መዋቅሮች፣ ልዩ ልዩ ዓይነት እርጥበትን መጠበቂያ መዋቅሮች እንዲሁም መሬትን ከሰውንና ከእንስሳት ንክኪ የመከላከል ሥራ መሠራቱን አመልክተዋል፡፡ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት በኩልም የአቮካዶ፣ የሙዝ፣ የፓፓያ፣ የአፕል እና የሌሎች የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች በስፋት መተከላቸውን ተናግረዋል።
በአስተዳደሩ በበጀት ዓመቱ ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ ጥረት ተደርጓል
Jul 19, 2026 116
ድሬደዋ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በበጀት ዓመቱ ከ7 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ በመሰብሰብ የነዋሪውን የልማት ጥያቄ ለመመለስ ጥረት መደረጉን የድሬደዋ አስተዳደር ገቢዎች ባለሥልጣን ገለጸ። የድሬደዋ አስተዳደር ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አብዱልሰላም መሐመድ (ዶ/ር) የተጠናቀቀውን የ2018 በጀት ዓመት የገቢ አሰባሰብና የአዲሱን በጀት ዓመት የገቢ ዕቅድ አስመልክተው ለኢዜአ ገለጻ አድርገዋል። በመግለጫውም በአስተዳደሩ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገትን ለማረጋገጥ የገቢ ምንጮችን ማስፋት ላይ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የገቢ አሰባሰቡን ዲጂታል በማድረግና ቅንጅታዊ አሠራርን በመተግበር በበጀት ዓመቱ ከ7 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን አንስተዋል። የተሰበሰበው ገቢ ከታክስና ከማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች መሆኑን ገልጸው፣ ይህም የዕቅዱን 78 ነጥብ 5 በመቶ ማሳካት መቻሉን ጠቁመዋል። ገቢው ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ2 ቢሊዮን 284 ሚሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለው አስታውቀዋል። የሚሰበሰበው ገቢ እየጨመረ በመምጣቱ የሕዝቡን የመሠረተ ልማት፣ የመንገድ፣ የጤና፣ የውኃና የገጠር መስኖ ጥያቄዎችን በተሻለ ፍጥነትና ጥራት ለመመለስ አስችሏል ብለዋል። ተግባሩን አጠናክሮ በማስቀጠልም በዘንድሮው በጀት ዓመት ከ13 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ መታቀዱን ተናግረዋል።   ከከተማዋ ግብር ከፋዮች መካከል አቶ ዮሴፍ አለባቸው እንዳሉት፤ ባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ የዘረጋው ዘመናዊ የግብር መሰብሰቢያ አሠራር ግብር ከፋዮች ኃላፊነታቸውን በወቅቱ እንዲወጡ አድርጓል። ግብር ከፋይ ወጣት ጽዮን ተከተል በበኩሏ፤ ግብርን መክፈል ለከተማዋ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት መሠረታዊ መሆኑን በመረዳት የዜግነት ግዴታዋን መወጣቷን አንስታለች።
በካፋ ዞን እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ከድህነት ለመውጣት ለሚደረገው ጥረት ስኬት ጥሩ ማሳያ ናቸው
Jul 18, 2026 716
ቦንጋ፤ ሐምሌ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በካፋ ዞን እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች ከድህነት ለመውጣት ለሚደረገው ጥረት ስኬት ጥሩ ማሳያ መሆናቸውን የብልጽግና ፓርቲ አመራሮች ገለጹ። የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽሕፈት ቤት እና የሁሉም ክልሎችና የከተማ አስተዳደር የፓርቲው ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ አመራሮች በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በካፋ ዞን ቦንጋ ከተማና አካባቢው የተለያዩ የልማት ስራዎችና አገልግሎት መስጫዎችን ጎብኝተዋል።   አመራሮቹ ከጎበኟቸው የልማት ስራዎች መካከል የእንስሳት ልማት፣ የሻይ ልማት፣ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት እና የካፋ ባህል ማዕከል ይገኙበታል። አመራሮቹ ከጉብኝቱ በኋላ በሰጡት አስተያየት በአካባቢው እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎች ሀገራዊ የልማት ኢንሼቲቮችን የሚደግፉና ብልፅግናን የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማዕከል የዘርፍ አስተባባሪ ሚኒስትር ዴኤታ ካሊድ አሉዋን፤ በካፋ ዞን እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች ከድህነት ለመውጣት ለሚደረገው ጥረት ስኬት ጥሩ ማሳያ መሆናቸውን ገልጸዋል። የውሽውሽ ሻይ ልማት ምርት ለሀገር ውስጥና ለውጭ ሀገራት እየቀረበ መሆኑ ከስራ እድል ፈጠራ ባለፈ ለውጭ ምንዛሪ ግኝት አቅም መሆኑን አንስተው በቀጣይ ልማቱን ወደ አርሶ አደሩ የማስፋት ስራ በትኩረት እንደሚሰራበት ተናግረዋል። መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት፣ በቦንጋ ከተማ በቅርብ ጊዜ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ቀልጣፋና ፈጣን አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ መመልከታቸውን አንስተዋል። የብልፅግና ፓርቲ የሀረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት አደረጃጃት ዘርፍ ሀላፊ ጃፈር ሱፊያን እና የብልፅግና ፓርቲ የሶማሌ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ምክትል ሀላፊ መሐመድ አብዱላሒ፣ ክልሉ በተፈጥሮ ሀብት የታደለ ሰፊ የመልማት አቅም ያለው መሆኑን ተናግረዋል።   በጉብኝታቸው በወተት ልማት የተጀመረው ስራ ተስፋ የሚሰጥና መስፋት ያለበት መሆኑን ጠቁመው አካባቢው ለእንስሳት ልማት ያለውን ምቹ ምህዳር መጠቀም እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል። የካፋ ባህል ማዕከል እና የአካባቢው ጥብቅ ደን ለቱሪዝም ምቹ በመሆኑ ሀብቱን ጠብቆ ለትውልድ ማስተላለፍ ይገባል ብለዋል። በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ምክትል ኃላፊ ሰላማዊት ጠብቀው፤ የጎበኘናቸው የልማት ስራዎችና የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ለተጀመሩ ዘርፈ ብዙ የለውጥ ተግባራት ትልቅ ተስፋ የሰነቁ ናቸው ሲሉ ተናግረዋል።   በክልሉ ያለው እምቅ የተፈጥሮ ሀብት በተቀናጀ፤ ፈጠራና ፍጥነት በታከለበት መልኩ ሰፊ ርብርብ ከተደረገበት በአጭር ጊዜ ውስጥ ብልጽግናን የማረጋገጥ ከፍተኛ አቅም እንዳለው ተመልክተናል ብለዋል።   አመራሮቹ በጉብኝታቸው ወቅት አረንጓዴ ዐሻራቸውንም አኑረዋል።
በምሥራቅ ቦረና ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ61 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል
Jul 18, 2026 484
ነገሌ ቦረና፣ ሐምሌ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በምሥራቅ ቦረና ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ61 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን የዞኑ የሥራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ የሥራ ዕድል ፈጠራ ቡድን መሪ አቶ ጎዳና ሳራ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ በዞኑ በሚገኙ ሁሉም ወረዳዎች ለ53 ሺህ 266 ወጣቶች የሥራ ዕድል ለማመቻቸት ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። በተሠራው ሥራም በዕቅድ ከተቀመጠው በላይ 61 ሺህ 111 ወጣቶችን በተለያዩ አራት ዋና ዋና የሥራ ዘርፎች ማሰማራት ተችሏል ብለዋል። እነዚህ ወጣቶች በ121 የኅብረት ሥራ ማኅበራት ተደራጅተው ወደ ሥራ የገቡ ሲሆን፣ ከእነዚህም መካከል 21 ሺህ 997ቱ ሴቶች ሲሆኑ፣ ከ6 ሺህ በላይ የሚሆኑት ደግሞ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመራቂዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህ የተመቻቸው የሥራ ዕድል የአርብቶ አደሩን የሥራ ባሕል በማጎልበትና በራስ አቅም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመዋል። የእንስሳት እርባታና ማድለብ፣ የአትክልትና ሥራሥር እንዲሁም የመስኖ ልማት፣ የማዕድን ልማት፣ የግብይትና ንግድ ሥራዎች፣ እና የእንጨትና ብረታብረት ውጤቶች ማምረት የሥራ ዕድሉ የተፈጠረባቸው ዘርፎች መሆናቸውን ገልጸዋል። የጽሕፈት ቤቱ የፋይናንስ አቅርቦት ባለሙያ አቶ ቦሩ ገልገሎ በበኩላቸው፤ ለበጀት ዓመቱ የሥራ ዕድል ፈጠራ ማስፈጸሚያ የሚሆን 464 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ የብድር አቅርቦት ታቅዶ እንደነበር አስታውሰዋል። በአጠቃላይ በበጀት ዓመቱ ከ578 ሚሊዮን 943 ሺህ ብር በላይ ብድር ማሰራጨት እንደተቻለም አመልክተዋል። ከፋይናንስ አቅርቦቱ በተጨማሪም በገጠር ከ1 ሺህ ሄክታር በላይ የማምረቻ ቦታ፣ በከተሞች ደግሞ 150 የመሸጫ ሼዶች ለተጠቃሚዎቹ ድጋፍ መደረጉን ባለሙያው ጠቅሰዋል። የሥራ ዕድሉ ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪው ወጣት ቢኒያም አምሳሉ፤ በእንጨትና ብረታብረት ሥራ መስክ ከሁለት ባልደረቦቹ ጋር በመደራጀት የቤትና የቢሮ ዕቃዎችን እያመረቱ መሆኑን ተናግሯል። የተደረገላቸው የማምረቻ ቦታና የብድር አገልግሎት ድጋፍ ሠርቶ ለመለወጥ ትልቅ አቅምና መነሳሳት እንደፈጠረላቸውም ገልጿል። በተመሳሳይ በእንጨት ሥራ ዘርፍ የተሰማራው ወጣት አብዲ ሁሴን በበኩሉ፤ ከሦስት ባልደረቦቹ ጋር በመሆን ሥራ ሳይንቁና ሳይመርጡ በቁርጠኝነት በመሥራት ሕይወታቸውን እያሻሻሉ እንደሚገኙ ገልጿል። የተመቻቸላቸው የብድር አገልግሎት ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን ከመደገፍ ባለፈ፣ ወደፊት ሌሎችንም ለመርዳት አቅደው እንዲሰሩ በር እንደከፈተላቸው አክሏል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም