ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በአፋር ክልል የተለያዩ ወረዳዎች የተገነቡ የመጠጥና የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ
May 19, 2026 29
ሰመራ ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦በአፋር ክልል የተለያዩ ወረዳዎች የተገነቡ የመጠጥና የመስኖ ልማት ፕሮጀክቶች ተመረቁ። ፕሮጀክቶቹን መርቀው ስራ ያስጀመሩት የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እና የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) ናቸው። የተመረቁት ፕሮጀክቶች ነዋሪዎች ከዚህ ቀደም ይገጥማቸው የነበረውን የመጠጥ ውሃ ችግር በዘላቂነት የሚፈቱ መሆኑ ተመላክቷል። በተለይም አርብቶ አደሮች ውሃ ለማግኘት ሩቅ አካባቢዎች በመሄድ ይደርስባቸው የነበረውን እንግልት የሚያስቀር መሆኑም ታውቋል። የመስኖ ፕሮጀክቱም የክልሉ አርብቶና አርሶ አደሮች በአካባቢው ያለውን ሰፊ መሬት በማልማት ምርታማ እንዲሆኑ የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። በመርሃ ግብሩ ላይ የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እና የመስኖ እና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) እና ሌሎችም የፌዴራልና የክልሉ የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል።
የመንገዱ መገንባት ቀደም ሲል ሲገጥመን የነበረን እንግልት አስቀርቶልናል - ነዋሪዎች
May 19, 2026 111
ቦንጋ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በአካባቢያቸው ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት የሆነው መንገድ ቀደም ሲል ሲገጥማቸው የነበረውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር ማስቀረቱን በኮንታ ዞን የኮንታ ኮይሻ ወረዳ ነዋሪዎች ተናገሩ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት በወረዳው የድልቢ ቀበሌ ነዋሪ አቶ በቀለ በተላ እና አቶ ብቸራ ቡሽራ ከዚህ ቀደም በአካባቢው መንገድ ባለመኖሩ ወደ ተለያዩ አካባቢዎች ለመንቀሳቀስ ይቸገሩ ነበር። በመንገድ እጦት ሕሙማንንም ሆኑ ነፍሰጡር እናቶችን ወደ ሕክምና ተቋም ለማድረስ እንዲሁም የግብርና ምርታቸውን ለገበያ ለማቅረብ ይቸገሩ እንደነበርም አስታውሰዋል። አሁን ላይ በአካባቢያቸው ተገንብቶ ለአገልግሎት የበቃው መንገድም ችግሩን መፍታቱን ጠቁመዋል። የመንገዱ ግንባታ ለፀጥታ ሥራ ትልቅ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ያነሱት ደግሞ ዋና ኢንስፔክተር ጊዲሶ አመሌ፣ በተለይ ችግሮች ሲከሰቱ ፈጥኖ ቦታው ደርሶ ምላሽ ለመስጠት እንዳስቻለም ተናግረዋል። ወይዘሮ ጤናዬ ሹምቡል በበኩላቸው፤ የመንገዱ አገልግሎት መጀመር በተለይ ሴቶችና ተማሪዎች ላይ ሲገጥም የነበረን ችግር ማስቀረቱን ጠቁመው፣ ወላድ እናቶች ወደጤና ተቋማት ሄደው እንዲወልዱ ማስቻሉን ገልጸዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ምክትል ሀላፊ ኢንጂነር ጌዲዮን እስጢፋኖስ፣ የክልሉ መንግስት የማህበረሰቡን የመንገድ መሰረተ ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ቀበሌን ከቀበሌ እና ከዋና መንገድ የማገናኘት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። በዓለም ባንክ ድጋፍ የገጠር ትስስር ለምግብ ዋስትና ፕሮግራም በ6 ዞኖች ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች በ865 ሚሊዮን ብር የመንገድ ግንባታ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል። ሰሞኑን ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው የ12 ኪሎ ሜትር ደልባ-አልፋ-ቶልካ መንገድ ፕሮጀክት አንዱ መሆኑንም ጠቅሰዋል። መንገዱ ከሦስት በላይ ቀበሌዎችን እርስ በርስ የሚያገናኝና ከ52 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደተደረገበትም ተናግረዋል። የመንገዱ መገንባት ከዚህ ቀደም በአካባቢው ማህበረሰብ ላይ ይደርስ የነበረውን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሌሎች ችግሮችን መፍታቱንም ኢንጂነር ጌድዮን ተናግረዋል።
በሀገራት መካከል የሚፈጠር ጠንካራ የኢኮኖሚ ትስስር አስተማማኝና ዘላቂ መረጋጋትን ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አለው
May 18, 2026 461
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦በሀገራት መካከል የሚፈጠር ጠንካራ የኢኮኖሚ ትስስር አስተማማኝና ዘላቂ መረጋጋትን ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳለው የጅቡቲ የኢኮኖሚ፣ ፋይናንስ፣ ኢንዱስትሪና ፕላኒንግ ሚኒስትር ኢልያስ ሙሳ ገለጹ። በሶማሌ ክልል ርዕሰ መዲና ጅግጅጋ ከተማ በቀጣናው ሰላም እና ደኅንነት ላይ ትኩረቱን ያደረገ ከፍተኛ ቀጣናዊ ፎረም እየተካሄደ ይገኛል። ’’ቀጣናዊ ተቋማትን ማጠናከር ለአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ ሰላም መረጋገጥ” በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀው ፎረም ቀጣናዊ መፍትሄዎች ለቀጣናዊ ችግሮች የሚለውን ዕሳቤ ማስተዋወቅ ዋና ዓላማው አድርጓል። ይህ መድረክ በውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት፣ በሰላም እና ፖለቲካዊ ምክክር ማዕከል፣ በሶማሌ ክልል መንግስትና ሌሎች አጋር አካላት በጋራ ተዘጋጅቷል። በጅግጅጋ ከተማ በተዘጋጀው ፎረም ላይ የኢትዮጵያን ጨምሮ የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት መንግስታት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ ምሁራን፣ ባለድርሻ አካላትና ተጋባዥ እንግዶች ታድመዋል። የጅቡቲ የኢኮኖሚ፣ ፋይናንስ፣ ኢንዱስትሪና ፕላኒንግ ሚኒስትር ኢልያስ ሙሳ፤ ጅቡቲና ኢትዮጵያ ከፍተኛ የንግድ ትስስር ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን አስታውሰው፤ በሀገራት መካከል የሚፈጠር ጠንካራ የኢኮኖሚ ትስስር አስተማማኝና ዘላቂ መረጋጋትን ለመፍጠር ትልቅ ማበረታቻ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ አካያ ለቀጣናዊ ብልፅግና እና ቀጣናዊ ሚዛንን ለመጠበቅ የኢትዮጵያ ሚና ታላቅ፣ ወሳኝና የማይተካ መሆኑን አክለዋል። የቀጣናዊ ራዕዩ ዋና ማዕከል የኢኮኖሚ ትስስር እና የኢኮኖሚ ኮሪደሮች መሆን እንዳለባቸውም ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ በኃይል ትስስር ረገድ ያሳየችውን ታላቅ መሪነትና የተግባር አፈጻጸም ያደነቁት ሚኒስትሩ፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ እና የፋይበር ኦፕቲክ የቴሌኮም መሠረተ ልማቶች የሁለቱን ሀገራት ኢኮኖሚና ህዝቦች በማገናኘት ረገድ ያላቸውን ጉልህ ሚና ገልጸዋል። በቀጣናው መጪው ጊዜ በጥንካሬ እንዲቃኝ፤ በጋራ ኃላፊነት፣ በኢነርጂ እንዲሁም በመሠረተ ልማት ትስስር ላይ የተመሰረተ ቀጠናዊ ትብብር መገንባት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ ቀጣናው የጋራ ውሳኔዎችን የሚያሳልፍበትና በተግባር ላይ ያተኮረ ትብብር የሚያመነጭበት ጠንካራ መድረክ እንደሚያስፈልገው በማሳሰብ፥ ጅቡቲ በአፍሪካ ቀንድ ሀገራት መካከል የሚደረጉ ውይይቶች ተቋማዊ ቅርፅ እንዲይዙ ሙሉ ድጋፏን እንደምትሰጥ አረጋግጠዋል።
ዘላቂ ሰላም በማስፈን የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ የቀጣናውን ተቋማት ቅንጅታዊ አሠራር ማጠናከር ይገባል
May 18, 2026 287
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦በምሥራቅ አፍሪካ ዘላቂ ሰላም በማስፈን የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ የቀጣናውን ተቋማት ቅንጅታዊ አሠራር ማጠናከር እንደሚገባ በኬንያ የጋሪሳ ካውንቲ ግዛት ገዥ ናቲፍ ጃማ አደም ገለጹ። በሶማሌ ክልል ርዕሰ መዲና ጅግጅጋ ከተማ በቀጣናው ሰላም እና ደኅንነት ላይ ትኩረቱን ያደረገ ከፍተኛ ቀጣናዊ ፎረም እየተካሄደ ይገኛል። ’’ቀጣናዊ ተቋማትን ማጠናከር ለአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ ሰላም መረጋገጥ” በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀው ፎረም ቀጣናዊ መፍትሄዎች ለቀጣናዊ ችግሮች የሚለውን ዕሳቤ ማስተዋወቅ ዋና ዓላማው አድርጓል። ይህ መድረክ በውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት፣ በሰላም እና ፖለቲካዊ ምክክር ማዕከል፣ በሶማሌ ክልል መንግስትና ሌሎች አጋር አካላት በጋራ ተዘጋጅቷል። በጅግጅጋ ከተማ በተዘጋጀው ፎረም ላይ የኢትዮጵያን ጨምሮ የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት መንግስታት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ ምሁራን፣ ባለድርሻ አካላትና ተጋባዥ እንግዶች ታድመዋል። የጋሪሳ ካውንቲ ግዛት ገዥ ናቲፍ ጃማ አደም በመድረኩ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ የምክክር ፎረሙ ወቅታዊና እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው፣ በምሥራቅ አፍሪካ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን ቀጣናዊ ተቋማትን ማጠናከር ቀዳሚ ተግባር መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። የምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና በተለያዩ ተፈጥሯዊ ጸጋዎች የታደለ፣ ስትራቴጂካዊ መልክዓ-ምድር ያለው እንዲሁም አፍሪካን ከመካከለኛው ምሥራቅና እስያ ጋር የሚያገናኘው የዓለም ትልቁ የባህር ላይ ንግድ መስመር መገኛ መሆኑን ገልጸዋል። ቀጣናው እምቅ የተፈጥሮ ሀብት፣ የበለጸገ ብዝኃ ባህልና ሰፊ የእንስሳት ሀብት ያለው ቢሆንም፤ ግጭት፣ የፖለቲካ አለመረጋጋት፣ ድርቅና መፈናቀል ተደጋጋሚ ፈተናዎቹ ሆነው መቀጠላቸውን ገዥው ጠቁመዋል። ምሥራቅ አፍሪካ የዕውቀት፣ የተፈጥሮ ሀብት አልያም የአመራር እጥረት የለበትም ያሉት ናቲፍ ጃማ፤ በአሁኑ ወቅት የጎደለው የተቀናጀ የፖለቲካ አመራርና ቀጣናዊ እሳቤ መሆኑን አስገንዝበዋል። ይህንን ችግር ለማቃለል የአየር ንብረት ተጋላጭነትን በጋራ መከላከል፣ ድንበር ተሻጋሪ የአርብቶ አደሮችን እንቅስቃሴ በቅንጅት መምራት እና የቀጣናዊ መሠረተ ልማት ኮሪደርን ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። በቀጣናው በአንድ ሀገር የሚከሰት ግጭትና አለመረጋጋት በቅጽበት በጎረቤት ሀገራት ላይ ተፅዕኖ እንደሚያሳድር የጠቀሱት ገዥው፤ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ከንግግር የዘለለ የተቋማት መዋቅራዊ ትስስርና ቅንጅታዊ አሠራር መፍጠር እንደሚገባ አሳስበዋል።
በክልሉ ገበያን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
May 18, 2026 189
ደብረ ማርቆስ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑ ተመለከተ። በደብረ ማርቆስ ከተማ ከ230 ሚሊየን ብር በላይ ወጭ የተገነባ የገበያ ማእከል ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል። በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማእረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳሃሉ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ በክልሉ ገበያን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ምርታማነትን የማሳደግ፣ የግብይት ስርአቱን የማሳለጥ፣ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ የማገናኘትና ህገ ወጥ ደላሎች ላይ ቁጥጥር የማጠናከር ተግባራት እየተከናወኑ ነው። በደብረ ማርቆስ ከተማ የተገነባው የገበያ ማእከል የጥረቱ አንድ አካል መሆኑን ጠቁመው ማእከሉ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ግብይቱን በማሳለጥ በኩል ሚናው የጎላ መሆኑን አመልክተዋል። የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር በዚህ በኩል እያደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን ጠቁመው በቀጣይም አስተዳደሩ በዘርፉ ለሚያከናውናቸው ተግባራት ድጋፍ እንደሚደረግ አስታውቀዋል። የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ተሾመ ዋለ በበኩላቸው፤ የገበያ ማእከሉ አምራቹና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመገበያየት የሚያስችል ነው ብለዋል። ማእከሉ ለከተማዋ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑንም አስታውቀዋል። የከተማ አስተዳደሩ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ ዮሴፍ መለሰ በበኩላቸው፤ የገበያ ማእከሉ ከ230 ሚሊየን ብር በላይ ወጭ የተገነባ መሆኑን ተናግረዋል። ማእከሉ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች የሚገበያዩበት በመሆኑ ለሸማቹ ህብረተሰብ የሚያስገኘው ጥቅም ከፍተኛ መሆኑን አስረድተዋል። የገበያ ማእከሉ መገንባት የንግድ ስርአቱን ለማዘመን የሚደረገውን ጥረት ያግዛል ያሉት ደግሞ የከተማው ንግድና ዘርፍ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሙሉጌታ አስረስ ናቸው። በምረቃ ስነ ስርአቱ ላይ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የጋራ አጀንዳችን ሆኖ ይቀጥላል-ተፎካካሪ ፓርቲዎች
May 18, 2026 173
ባህር ዳር፤ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦የብሄራዊ ጥቅምና የሀገር ህልውና ጉዳይ የሆነው የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ በፅኑ አቋም የምንሰራበት የጋራ አጀንዳችን ሆኖ ይቀጥላል ሲሉ በአማራ ክልል የሚንቀሳቀሱ ተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች ገለጹ። ኢትዮጵያ የባህር መውጫ መግቢያ የተነፈጋት ሀገር ሆና መቀጠል የማትችልባቸው የተለያዩ አሳማኝ እውነታዎች ስለመኖራቸውም የፓርቲዎቹ አመራሮች አንስተዋል። በአንድ ወቅት የባህር በር ባለቤት የነበረችው ኢትዮጵያ ምክንያቱ በውል በማይታወቅ ሁኔታ ከባህር እንድትርቅና የተቆለፈባት ሀገር እንድትሆን ተደርጓል። ከቀይ ባህር በቅርብ ርቀት ላይ እያለች የኢፍትሃዊና ምክንያት አልባ በሆነ አግባብ ኢትዮጵያ ከባህር እንድትገለል የተደረገበት ጉዳይ የብዙ አመታት ቁጭት ቢሆንም አሁን ላይ ምላሽ የሚሻ የትውልድ ጥያቄ ሆኖ መጥቷል። በመሆኑም የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የፖለቲካም ይሁን ሌላ ልዩነት ሳይገድበው በጋራ የቆምንለት የሀገር ህልውና ጉዳይ ነው ሲሉ የፓርቲ አመራሮች ተናግረዋል። የአማራ ዲሞክራሲ ሃይሎች ንቅናቄ (አዴሃን) ስራ አስፈፃሚ አባል አዲሱ ጉልላት፤ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ በተቃርኖ ሊቆም የሚችል የፖለቲካ አቋም መኖር እንደሌለበት የጸና እምነት አለን ሲሉ ገልጸዋል። የሀገር ህልውና እና የብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ የሆነው የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ መስራት የሁላችንም ግዴታ ነው ብለዋል። በመሆኑም የሀገር ህልውና እና የብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ የሆነው የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ መስራት የጋራ አጀንዳችን ሆኖ ይቀጥላል ሲሉ አረጋግጠዋል። የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) ምክትል ሊቀመንበር መልካሙ ፀጋየ፤ ፓርቲያቸው በሀገር ብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ ወደ ኋላ ሳይል እየሰራ መሆኑንና በቀጣይም አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችበት ኢፍትሃዊነት ሁላችንም የምንቆጭበት በመሆኑ ለምላሹ ያለልዩነት በጋራ የምንሰራበት ታሪካዊ ምእራፍ ላይ እንገኛለን ብለዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በታሪክ፣ በመልክአ ምድርም ይሁን በዓለም አቀፍ ህግ ተቀባይነት ያለው ፍትሃዊ ጥያቄ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም የብሄራዊ ጥቅምና የሀገር ህልውና ጉዳይ የሆነው የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ በፅኑ አቋም የምንሰራበት የጋራ አጀንዳችን ሆኖ ይቀጥላል ሲሉ ተናግረዋል። የኢትዮጰያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የሰሜን ኢትዮጵያ አስተባባሪ ሃይለማርያም ብርሃኑ፤ የባህር በር ለኢትዮጵያ አማራጭ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም ፓርቲያቸው ይህንን ሀገራዊ የህልውና ጉዳይ በፅኑ አቋም አጀንዳው አድርጎ የሚሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል። የብሄራዊ ጥቅምና የሀገር ህልውና ጉዳይ የሆነው የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በዚህ ትውልድ ምላሽ ማግኘት ያለበት ብሄራዊ አጀንዳ መሆኑንም አጽኖት ሰጥተዋል።
በአማራ ክልል ሰላምን በማስጠበቅ ህብረተሰቡን የልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የተሰራው ስራ ውጤታማ ነው
May 18, 2026 124
ሐይቅ፤ ግንቦት 10/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ሰላምን በማስጠበቅ ህብረተሰቡን የልማቱ ተጠቃሚ ለማድረግ የተሰራው ስራ ውጤት ማስገኘቱን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለፁ። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በምረቃው እንደገለፁት፣ የክልሉን ሰላም በማጽናት በተለያዩ አካባቢዎች በርካታ የልማት ስራዎችን ማከናወን ተችሏል። በዚህም እንደ ሐይቅ ከተማ ያሉ በርካታ የቱሪዝም፣ የግብርና እና ሌሎች ፀጋዎች ያሏቸው ከተሞች የብልጽግና ጉዞ መጀመራቸው የሚበረታታ ነው ብለዋል። በከተማዋ በቅርቡ በገበታ ለትውልድ የተገነባው የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት በአጭር ጊዜ የከተማዋንና የአካባቢውን ገጽታ በመቀየር ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረጉን ገልጸዋል። በተጨማሪም በአጭር ጊዜ ተገንብቶ ዛሬ የተመረቀው የኮሪደር ልማት ለከተማው ቱሪዝም ተጨማሪ የመስህብ አቅምና ውበትን የፈጠረ ነው ብለዋል። ህብረተሰቡ አንድነቱንና ሰላሙን በመጠበቅ የተጀመረውን ልማት በማስቀጠል ብልፅግናውን ለማረጋገጥ ከአካባቢው መስተዳድር ጋር ተባብሮ መስራት እንዳለበትም አሳስበዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አሊ መኮነን፣ በበኩላቸው ህብረተሰቡን በማሳተፍ የዞኑን ሰላም ማስጠበቅ በመቻሉ ለልማት ስራዎች ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ብለዋል። በዞኑ የተለያዩ ፕሮጀክቶች እየተገነቡና እየተመረቁ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ጠቁመው በሐይቅ ከተማ ዛሬ ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው የኮሪደር ልማት የዚሁ ማሳያ ነው ያሉት። የኮሪደር ልማቱ ከሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ጋር ተደምሮ ለከተማዋ ተጨማሪ ውበትን የፈጠረ መሆኑን ጠቅሰው ይህም ምቹ የመኖሪያ አካባቢን ለመፍጠርና ጎብኚዎችን ለመሳብ ያስችላል ብለዋል። የሐይቅ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ከድር መሀመድ በበኩላቸው፣ በከተማው በ130 ሚሊየን ብር የተገነባው ኮሪደር ልማት በአጭር ጊዜ በጥራት ተጠናቆ ለምረቃ መብቃቱን ተናግረዋል። የኮሪደር ልማቱ የእግረኛና የሳይክል መንገድን ጨምሮ ሌሎችንም የመዝናኛ ስፍራዎች ያካተተ መሆኑን አብራርተዋል።
በኦሮሚያ ክልል በመኸር እርሻው 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ሄክታር መሬት በሩዝ ሰብል ይለማል
May 18, 2026 108
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በተያዘው የመኸር እርሻ 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ሄክታር መሬት በሩዝ ሰብል እንደሚለማ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ በሪሶ ፈይሳ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ክልሉ ለሩዝ ልማት ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በተሠራው ሥራ ተጨባጭ ውጤት እየታየ ነው። በክልሉ በ2014/15 የምርት ዘመን በ100 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ተጀምሮ የነበረው የሩዝ ልማት፣ አሁን ላይ በከፍተኛ ሁኔታ በማደግ የሕዝቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ይገኛል ብለዋል። ይህ የሩዝ ልማት በተለይም በምዕራብ ኦሮሚያ አካባቢ በሚገኙ ዞኖች በስፋት እየለማ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል። ባለፈው ዓመት 1 ነጥብ 2 ሚሊየን ሄክታር መሬት ላይ ከለማው የሩዝ ሰብል ወደ 63 ሚሊየን ኩንታል ምርት መገኘቱን ጠቁመው በ2018/19 የምርት ዘመን 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ሄክታር መሬት በማልማት 100 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለማግኘት ታቅዷል ብለዋል። በክልሉ በሩዝ ልማት ውጤታማ ለመሆን አመቺ የሆኑ አካባቢዎች በጥናት ተለይተው ኢኒሼቲቩ ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል ነው ያሉት። አሁን ላይ ለአርሶ አደሩ የሚያስፈልገው ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በበቂ ሁኔታ የቀረበ ሲሆን፤ የባለሙያ የቅርብ ድጋፍና ክትትልም እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ከሩዝ ልማቱ አምራች አርሶ አደሮች የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ ምርቱን ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መጥቷል ብለዋል። በልማቱ ዙሪያ የአርሶ አደሩ ተነሳሽነት በየጊዜው እያደገ የመጣ ሲሆን፤ ዘመናዊ የግብርና ቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲሰፋና አርሶ አደሩም በሩዝ ልማት ላይ የተሻለ ልምድ እያገኘ መሆኑን ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ልማት ፕሮግራም ሥር ታላላቅ ሀገራዊ ስኬቶች ተመዝግበዋል
May 18, 2026 103
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ልማት ፕሮግራም ሥር ታላላቅ ሀገራዊ ስኬቶች መመዝገባቸውን የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ትንተና ቢሮ ኃላፊ አባስ መሐመድ ገለጹ። ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው ሀገራዊ ጉባኤ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት እየተካሄደ ነው። በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ትንተና ቢሮ ኃላፊው አባስ መሐመድ፣ ስለ ኢትዮጵያ የመረጃ ሉዓላዊነት ጉዞ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም ሕጋዊ ዕውቅና ያላቸው፣ በሳይንሳዊ ስልት የተዘጋጁ እና ለሕዝብ ክፍት የሆኑ ይፋዊ ስታቲስቲክስ እንዴት ጥሬ መረጃዎችን ወደ ተጨባጭ ማስረጃ፣ ማስረጃዎችን ደግሞ ወደ መልካም አስተዳደር እንደሚቀይሩ ገልጸዋል። ያለ መረጃ የሚታቀድ ትልም ምኞት ብቻ መሆኑን የጠቆሙት ኃላፊው፤ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የአሥር ዓመቱ የልማት ዕቅድ እምነት የሚጣልባቸውና የኢትዮጵያውያን ባለቤትነት የተረጋገጠባቸውን መረጃዎች (ቁጥሮች) እንደሚሹ ተናግረዋል። በተጨማሪም በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ልማት ፕሮግራም ሥር የተመዘገቡ ታላላቅ ስኬቶችን አጉልተው ያሳዩ ሲሆን ከእነዚህም መካከል ሙሉ በሙሉ ይፋ የተደረገውን የሥነ-ህዝብ እና ጤና ጥናት፣ ሙሉ በሙሉ በኢትዮጵያውያን የመንግሥት ሠራተኛ ባለሙያዎች የተከናወነውንና ከተለመደው ያደገውን የተቀናጀ የቤተሰብ ጥናት፣ እንዲሁም በግብርና ቆጠራ እና በኢኮኖሚ ተቋማት ቆጠራ ላይ የተመዘገቡ ዋና ዋና እመርታዎችን ጠቅሰዋል።
በመንግስት በተወሰዱ ቁርጠኛ እርምጃዎች የሀገሪቱን ሉዓላዊነትና የፖሊሲ ነፃነት የሚያረጋግጥ የመረጃ ሥርዓት መገንባት ተችሏል - ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር)
May 18, 2026 115
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ መንግስት በወሰዳቸው ቁርጠኛ እርምጃዎች የሀገሪቱን ሉዓላዊነትና የፖሊሲ ነፃነት የሚያረጋግጥ የመረጃ ሥርዓት መገንባት መቻሉን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) ገለጹ። ''የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነፃነት'' በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው ሀገራዊ ጉባኤ፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት እየተካሄደ ይገኛል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) በጉባኤው ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር ቀደም ሲል ሀገራዊ የመረጃ ሥርዓቱ በራስ አቅም ላይ ያልተመሠረተ በውጭ ድጋፍ ጥገኝነት ላይ የቆየና የተዓማኒነት ጥያቄዎች የሚነሱበት እንደነበር አንስተዋል። ከዚህ ለመላቀቅ በተደረጉ ቁርጠኛ እርምጃዎች የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርምና የ10 ዓመቱን የልማት ዕቅድ አፈጻጸም መከታተል የሚያስችሉ እንደ የተቀናጀ የቤተሰብ ጥናት፣ የቱሪዝም መረጃ እና የቢዝነስ ድርጅቶች ቆጠራ ያሉ የተለያዩ የዳሰሳ ጥናት በማድረግና በዲጂታል ሥርዓት በማዘመን እንዲሁም ለመረጃ ልማት ከፍተኛ ኢንቨስትመንት በማድረግ የመደመር እሳቤን መሠረት ያደረገ የመረጃ ተኮር ፖሊሲ አመራርና ውሳኔ ሰጪነትን ማረጋገጥ መቻሉን አመልክተዋል። ይህ ዓይነቱ የሪፎርም ውጤት፤ መረጃዎች በኢትዮጵያ ልጆች እንዲሰበሰቡና እንዲተነተኑ በማድረግ የሀገሪቱን ሉዓላዊነትና የፖሊሲ ነፃነት የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል። ብሔራዊ ጥቅምን፣ የዜጎችን ደኅንነትና የልማት ትልሞችን በጽኑ መሠረት ላይ በመገንባት ከተለመደው የምላሽ ሰጭነት አሠራር ወደ ቅድመ-ትንበያ መሸጋገር የሚያስችል ዘላቂ ተቋማዊ ዐቅም መፈጠሩን ገልጸዋል።
በጉራጌ ዞን የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች ልማት የአርሶ አደሩን ምርታማነት አሳድጓል
May 18, 2026 91
ወልቂጤ፣ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ):-በጉራጌ ዞን የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በማልማት ምርታማነታቸውን ማሳደግ እንደቻሉ አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ እኖር ወረዳ የከረቤድ ቀበሌ አርሶ አደር ሞሳ በሽር የተሻሻለ የቡና ተክል በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ ናቸው። በመጪው ክረምት የሚተከል ከ1 ሺህ በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን ለመትከል የጉድጓድና የተፈጥሮ ማዳበሪያ እያዘጋጁ መሆናቸውን ጠቁመዋል። የቡና ልማትን ለማስፋፋትም በመንግስት በኩል ምርታማ የሆኑና በሽታን መቋቋም የሚችሉ የቡና ችግኞች ከማግኘታቸው ባለፈ የባለሞያ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑን ገልጸዋል። በአበሽጌ ወረዳ ጣጤሳ ቀበሌ አርሶ አደር ሙርሺዳ አብዶ በበኩላቸው ከመንግስት በድጋፍ የተረከቧቸውን የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች በሦስት ዓመት ጊዜ ውስጥ ምርት በመስጠት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። የተሻሻሉት የቡና ዝርያዎች በምርትና በሽታን በመከላከል ረገድ ውጤታማ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ ሥራውን ይበልጥ ለማሳካትም በጥላ ዛፍ ሥር በመከለልና የተፈጥሮ ማዳበሪያ በመጠቀም እንክብካቤ እያደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። የቡና ልማቱን አጠናክሮ ለማስቀጠልም ዘንድሮም 250 የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን ለመትከል ጉድጓዶችን በመቆፈር የተከላ ጊዜውን እየጠበቁ መሆናቸውን ገልጸዋል። የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ በበኩላቸው፣ በዞኑ በምርታማነታቸው የተረጋገጡ የቡና ዝርያዎች ለአርሶ አደሩ መቅረባቸው ከዘርፉ የሚገኘውን ውጤት እያሳደገው ነው። ለዚህም የዞኑን የቡና ማሳ ሽፋን 55 ሺህ 400 ሄክታር መድረሱን የገለጹት አቶ አበራ፣ ምርታማነትም በአማካይ በሄክታር ከስምንት ኩንታል በላይ መድረሱን ጠቅሰዋል። የቡና ልማቱን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማስፋት በዘንድሮ ዓመትም የተሻሻለ የቡና ችግኝ ተከላ ሥራ መጀመሩን ገልጸዋል።
በገላን ጉራ ያረፈው አሻራችን የኢንዱስትሪ ፓርክ ብቻ ሳይሆን፣ የአካባቢውን ገጽታ እና የነዋሪዎቹን ሕይወት ሙሉ በሙሉ ከስር መሠረቱ የለወጠ ነው
May 18, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018(ኢዜአ)፦ በገላን ጉራ ያረፈው አሻራችን የኢንዱስትሪ ፓርክ ብቻ ሳይሆን፣ የአካባቢውን ገጽታ እና የነዋሪዎቹን ሕይወት ሙሉ በሙሉ ከስር መሠረቱ የለወጠ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ያስተላለፉት ሙሉ መልዕክት እንደሚከተለው ቀርቧል ገላን ጉራ የብልጽግና አሻራ! የመዲናችን የብልጽግና ጉዞ ስፋትና ጥልቀት የሚለካው፣ የከተማዋን እምብርት በማስዋብ ብቻ ሳይሆን፣ ትናንት በአግባቡ ያልተጠቀምንባቸውን ሀብትና አካባቢዎችን ዓይናችንን ገለጥ በማድረግ ተመልክተን የልማትና የዕድገት ማዕከል በማድረግም ጭምር ነው። ከ5 ዓመት በፊት፣ ምንም የሚታይ መሠረተ ልማት ያልነበረው የገላን ጉራ አካባቢ፣ ዛሬ ላይ የታሪክ ምዕራፉ ተቀይሮ የከተማችንን ሁለንተናዊ የልማት ከፍታና መዋቅራዊ ሽግግር የሚያሳይ የኢኮኖሚና የማኅበራዊ መስተጋብር ማዕከል ሆኗል። ዛሬ በዚህ ስፍራ ያረፈው አሻራችን የኢንዱስትሪ ፓርክ ብቻ ሳይሆን፣ የአካባቢውን ገጽታ እና የነዋሪዎቹን ሕይወት ሙሉ በሙሉ ከስር መሠረቱ የለወጠ ነው። ለአብነትም:- 1. በአዲስ አበባ የመጀመሪያው እና ትልቁ ባለ 325 ሜትር ርዝመትና 60 ሜትር ስፉት ዘመናዊ ድልድይ፣ 2. 21 ነጥብ 73 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው (ቃሊቲ ቀለበት -ቱሉዲምቱ እና ቃሊቲ ቀለበት - ቂሊንጦ አደባባይ) የኢትዮጵያ የንግድ ኮሪደርን ያሳለጠ እና ቀጥታ ከአየር መንገድ ካርጎ የሚያገናኝ ዘመናዊ የመንገድ መሠረተ ልማት፣ 3. የከተማችንን የመኖርያ ቤት አቅርቦት ችግር ለማቃለል አዲስ ከተማን የመገንባት ያህል የሆነ 60 ሺህ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ፣ 4. ከካዛንቺስ አካባቢ ለልማት ለተነሱ ነዋሪዎቻችን የገነባነው ምቹና የተቀናጀ ዘመናዊ የመኖሪያ መንደር የሚገኝበት፣ 5. የኅብረተሰባችንን ጤና በላቀ ደረጃ ለመጠበቅ በከተማችን በትልቅነቱ ቀዳሚ የሆነው የገላን ትሯማ ሆስፒታል ግንባታ፣ 6. በአካባቢው ለዚሁ ልማት ለእርሻ ሲጠቀሙበት የነበረውን መሬት ለለቀቁልን አርሶ አደሮች የተቀናጀ ዘመናዊ የግብርና ልቀት ማዕከል ግንባታ፣ 7. መንፈስን የሚያድሱ ሰፋፊ አረንጓዴ ስፍራዎችና ፓርኮች፣ 8. የስፖርት ማዘውተሪያዎችና የልጆች መጫወቻዎች፣ ለእናቶች ሰፊ የስራ ዕድል የሚፈጥር የእንጀራ ፉብሪካ ግንባታና የመሳሰሉት የብልፅግና አሻራዎች ደምቀው አካባቢውን ከመሐል ከተማ የበለጠ ተመራጭ አድርገውታል።
ልማት የማያገኙ የነበሩ አካባቢዎችን ፍትሐዊ ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል - ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)
May 17, 2026 377
ቦንጋ ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ባለፉት አምስት አመታት ልማት የማያገኙ የነበሩ አካባቢዎችን ፍትሐዊ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕስ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) አስታወቁ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በኮንታ ዞን ኮይሻ ወረዳ 142 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገባቸው የንጽህ መጠጥ ውሃና የመንገድ ፕሮጀክቶችን መርቀው ስራ አስጀምረዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በመርሃ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ በክልሉ ባለፉት አምስት አመታት ከልማት የራቁ አካባቢዎችን ፍትሀዊ ተጠቃሚ ለማድረግ የተለያዩ የልማት ስራዎች ተከናውነዋል። በዚህም የኮንታ ኮይሻ ወረዳ አንዱ መሆኑንና ማህበራዊ ተቋማትን በማዳረስ ህብረተሰቡ አገልግሎቶችን በአቅራቢያው እንዲያገኝ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የክልሉ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ሀላፊ ኢንጂነር በየነ በላቸው በበኩላቸው፤ ክልሉ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ የህብረተሰቡን የንጹህ መጠጥ ውሃ ፍላጎት ለማሟላት የተለያዩ የውሀ ተቋማት ተገንብተዋል ብለዋል። በዚህም ክልሉ ሲመሰረት የነበረውን ንፁሃ የመጠጥ ውሃ ሽፋን በእጅጉ ከፍ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። ዛሬ ለተመረቀው የኮንታ ኮይሻ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ግንባታ 90 ሚሊዮን ብር ወጪ መደረጉን አስታውቀዋል። የኮንታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ታከለ ተስፉ በበኩላቸው፤ በዞኑ ባለፉት አምስት ዓመታት የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት በቅተዋል ብለዋል። ዛሬ የተመረቁ ፕሮጀክቶችም ለማህበረሰቡ የጎላ ጠቀሜታ የሚሰጡ መሆናቸውን ጠቁመዋል ። የኮንታ ኮይሻ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማርቆስ ወንድሙ፤ የውሀ ተቋሙ የኮይሻ ከተማ ማህበረሰብ ጥያቄን የመለሰ መሆኑን ተናግረዋል ። በለውጡ መንግስት የኮይሻ ወረዳ የውሃ፣ የመንገድ፣ የመብራት የመሳሰሉ መሰረተ ልማቶች ተጠቃሚ መሆኗን ጠቁመዋል። በተመሳሳይ በወረዳው 52 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገበት የደለባ አልፋ ቶልካ የመንገድ ፕሮጀክትም ተመርቋል። መንገዱ 12 ነጥብ 1 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለውና ከሶስት በላይ ቀበሌዎችን የሚያገናኝ መሆኑ ተመላክቷል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ሀላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በክልሉ ለማህበረሰቡ የልማት ጥያቄ ምላሽ የመስጠት ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል
May 17, 2026 277
ቡኢ ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ለማህበረሰቡ የልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ምላሽ የመስጠት ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ። ርዕሰ መስተዳድሩ በምስራቅ ጉራጌ ዞን ሶዶ ወረዳ ከ56 ሺህ 750 በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሁለት ጤና ጣቢያና አንድ አጠቃላይ ጤና ኬላን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በወቅቱ እንደገለጹት የክልሉ መንግስት የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እያከናወናቸው ባሉ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ነው። በክልሉ ለማህበረሰቡ የልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ምላሽ እየተሰጠ መሆኑን ጠቁመው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመላክተዋል። ለዚህም ስኬት ከማህበረሰቡ የሚነሱ የጤና ተቋማት፣ መንገድንና መብራት ጨምሮ ሌሎች የልማት ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ ምላሽ የመስጠት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። የክልሉ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ማሙሽ ሁሴን በበኩላቸው፤ በምስራቅ ጉራጌ ዞን ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት የተደረጉ የጤና ተቋማት ለማህበረሰቡ የጤና አገልግሎትን በብቃት ለመስጠት አጋዥ ናቸው ብለዋል። በመንግስትና በማህበረሰብ ተሳትፎ ከ200 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸዉ የአዴሌና የሱተን ጤና ጣቢያ እንዲሁም የዱግዳ ጤና ኬላ ከ56 ሺህ 750 በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርጉ ጠቁመዋል። የእናቶችንና የህፃናት ሞት ለመቀነስ የተያዘውን ግብ ለማሳካት የጤና ተቋማቱ መጠናቀቅ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ገልፀዋል። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሙስጠፋ ሀሰን እንደገለፁት፤ የጤና ተቋማቱ ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸው መንግስት ጤናው የተጠበቀ ማህበረሰብን ለመፍጠር የያዘውን አቅጣጫ እውን የሚያደርግ ነው። በዞኑ ተላላፊና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎችን ለመከላከልና ጤናማ ማህበረሰብ ለመፍጠር እንደሚያግዝም ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደም በአካባቢው የጤና ተቋም ባለመኖሩ የህክምና አገልግሎት ለማግኘት ረጅም ርቀት ለመጓዝ ይገደዱ እንደነበር የገለጹት ደግሞ በሶዶ ወረዳ ሱተን ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ወርቅነሽ አበበ ናቸው። ዛሬ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የጤና ጣቢያ ከዚህ ቀደም የህክምና አገልግሎት ለማግኘት ወደ ሌላ ስፍራ በመጓዝ ይደርስባቸው የነበረውን እንግልት እንደሚያስቀር ገልጸዋል። በሌላ በኩል ርዕሰ መስተዳድሩ በሶዶ ወረዳ ሪፌንሶ ከተማ ለሚካሄደው የማህበረሰብ መድሀኒት ቤት ግንባታ ስራ ማስጀመሪያ የመሰረተ ድንጋይ ያኖሩ ሲሆን በመርሐ ግብሩ የክልል፣ የዞንና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮችና ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚሰጣቸው የላቁ አገልግሎቶች የሚደነቁ ናቸው
May 17, 2026 175
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚሰጣቸው ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶች ከፍተኛ አድናቆት የሚቸረው መሆኑን አየር መንገዱ ባዘጋጀው የሩጫ ውድድር ላይ የተሳተፉ የውጭ ሀገራት ዜጎች ገለጹ። ተሳታፊዎቹ የዋና ከተማዋ የአዲስ አበባ ዘመናዊና ፈጣን እድገት እጅግ አስደናቂ መሆኑንም አንስተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ 80ኛ አመት ምስርታ በዓልን በማስመልከት ባዘጋጀው የሩጫ ውድድር ላይ ከተለያዩ የዓለም ሀገራት የመጡ በርካታ እንግዶች ተሳትፈዋል። ተሳታፊዎቹ ለኢዜአ እንደገለጹት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለፉት ስምንት አስርት ዓመታት ያስመዘገባቸው ስኬቶች አስደናቂ ናቸው። ከአሜሪካ የመጣችውና በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው ካቲ ቴለር በመላው አውሮፓ፣ አሜሪካና በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች ለምታደርጋቸው ጉዞዎች ሁልጊዜ የምትጠቀመው የኢትዮጵያ አየር መንገድን መሆኑን ገልጻለች። አየር መንገዱ በሀገር ውስጥ፣ በአህጉሩና በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ ስም ያለውና እጅግ አስደሳች አገልግሎት የሚሰጥ ተቋም መሆኑን በመግለጽ አድናቆቷን ችራለች። የሩጫ ውድድሩ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ህዝብ የተሳተፈበትና እጅግ ደማቅ ዝግጅት እንደነበር የጠቀሰችው አሜሪካዊቷ፤ የኢትዮጵያ ህዝብ እንግዳ ተቀባይ መሆኑንም ገልጻለች፡፡ ይህ ደግሞ በጣም የሚያስደስትና የሚያኮራ ነው ብላለች። የአዲስ አበባን ፈጣን ለውጥ በተመለከተም በየጊዜው አዳዲስ ግንባታዎችን፣ ዘመናዊ ሕንፃዎችንና አዳዲስ መሰረተ ልማቶችን መመልከቷን አስታውቃለች፡፡ ከብራዚል የመጣችው ተሳታፊ ሊዲያ ቡርኖ በበኩሏ፤ ይህ በኢትዮጵያ የመጀመሪያዋ ውድድር እንዳልሆነና ቀደም ሲል በሐዋሳ ግማሽ ማራቶን ላይ መሳተፏን አስታውሳለች። ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ውበት የታደለች ሀገር መሆኗን የጠቆመችው ብራዚላዊቷ፣ ዋና ከተማዋ አዲስ አበባም በፈጣን እድገት ላይ የምትገኝ ሳቢ ከተማ መሆኗን ገልጻለች። ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በተደጋጋሚ መጓዟን እና የአየር መንገዱ አገልግሎት እጅግ አስደናቂና በጣም የሚያኮራ መሆኑን ጨምራ ተናግራለች። ሁልጊዜ ከጃፓን ወደ ኢትዮጵያ ስንመጣ ቀዳሚ ምርጫችን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው፤ የበረራ አባላቱን ጨምሮ እያንዳንዱ የአየር መንገዱ ሰራተኛ ሙያዊ ስነ ምግባሩ የላቀ ነው ሲል የገለጸው ደግሞ ጃፓናዊው ዲያላስ ኒዩሳኮ ነው።
የጎዴ ማዳበሪያ ፋብሪካን ከተያዘለት ጊዜ ቀድሞ ለማጠናቀቅ አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 17, 2026 386
አዲስ አበባ፤ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፡- በጎዴ እየተገነባ የሚገኘውን የማዳበሪያ ፋብሪካ በአጠረ ጊዜ ውስጥ አጠናቅቀን የኢትዮጵያን አንዱን ቁልፍ ችግር እንፈታለን የሚል እምነት ይዘን እየሠራን ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ዛሬ ከአሊኮ ዳንጎቴ ጋር በመሆን በጎዴ ተገኝተው የማዳበሪያ ፋብሪካው የግንባታ ሥራ የደረሰበትን ደረጃ ለመገምገም የፕሮጀክት ስፍራውን ጎብኝተዋል። ከጉብኝታቸው በኋላ በሰጡት ማብራሪያም፤ በዚህ ቦታ መገኘታችን ይህ ፕሮጀክት በቅርበት የምንከታተለው፣የምናየው፣ የምንመራው፣ችግሮች ካሉ እየቀረፍን ከተቻለ አፍጥነን ካልሆነም ባልነው ጊዜ ለመጨረስ ያለንን ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል። በመላው የፕሮጀክቱ ስፍራ የሚታየው የሥራ ሂደት ፍጥነት አበረታች መሆኑንም አረጋግጠዋል። ከጥቂት ወራት በፊት ከዳንጎቴ ጋር የነበረን ስምምነት በጎዴ 3 ሚሊየን ቶን ማዳበሪያ ማምረት የሚችል ፋብሪካ መገንባት ነበር ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤በዚሁ ወቅትም ለሕዝባችን የገባነው ቃል ፋብሪካው በ40 ወራት ይጠናቀቃል የሚል ነበር ብለዋል። አሁን እየሠራን ያለነው ግን በተቻለ መጠን ከ40 ወራት ባነሰ ጊዜ ለማጠናቀቅ ነው፤በዚህም መሠረት ለእኛም ገበያ ከእኛ የሚተርፍ ካለም ለውጭ ገበያ ለመጠቀም እየሠራን ነው ሲሉ አስረድተዋል። ያኔ ሐሳብ ነበር፤አሁን ግን በተግባር እየተሠራ ነው፤ቢበዛ ከአራት ወራት በኋላ ስንመጣ አብዛኛው የመኖሪያ ቤት ግንባታ ይጠናቀቃል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)፤ በዚህም መሠረት ለ5 ሺህ ሰው የሚሆን የመኖሪያ ቤት ግንባታ (ትንሽ መንደር) ይሠራል ነው ያሉት። በአካባቢው ያለውን ውኃ ወደ ግንባታ ስፍራው አካባቢ የማምጣት፣ ከፍተኛ ቦታዎችን ዝቅ የማድረግና ዝቅተኛ ቦታዎችን ከፍ አድርጎ የማስተካከል ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝም አመልክተዋል። ለቀጣይ ሥራውም በርካታ ሪሶርስ (ግብዓት) ተገዝቶ እየመጣ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል። በአጠረ ጊዜ ውስጥ የማዳበሪያ ፋብሪካውን አጠናቅቀን የኢትየጵያን አንዱን ቁልፍ ችግር እንፈታለን የሚል እምነት አለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አሊኮ ዳንጎቴ በጣም ቁርጠኛ ሰው መሆናቸውን፤በገቡት ቃል መሠረት ገንዘባቸውን፣ጊዜያቸውን እና ሙያተኞችን በስፍራው ማቅረባቸውን ተናግረዋል። የቅርብ ክትትልና ድጋፍ በማድረግ ፕሮጀክቱን በማሳካት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ዋነኛውን ችግር ለመፍታት እየተጉ መሆናቸውን በመጠቆም፤ እስካሁን በጣም ደስ የሚል ሥራ ማየታቸውን አንስተዋል። በዚሁ መልክ የክልሉ ብሎም የፌዴራል መንግሥት የቅርብ ክትትልና ድጋፍ እያደረጉ እንዲጠናቀቅ ካደረግን በጣም ትልቅ ችግር የሚፈታ ፕሮጀክት ይሆናል የሚል ሙሉ እምነት አለኝ ብለዋል። ጎዴ አካባቢ የምናደርጋቸው ኢንቨስትመንቶች ተደማምረው በኢትዮጵያ አየር መንገድ ደረጃ ከፍተኛ ገቢ ለኢትዮጵያ የሚያስገቡ ናቸው ሲሉም አስረድተዋል። በአካባቢው እየተከናወኑ ያሉት ቀላል ኢንቨስትመንት እንዳልሆኑ ገልጸው፥ አሊኮ ዳንጎቴ ብቻ ከ3 ቢሊየን ዶላር በላይ ነው እዚህ የሚያፈስሱት ብለዋል። በአጠቃላይ በጣም ትልቅ የሀገርን መልክ፣ቁመና እንዲሁም የኢኮኖሚ ዐቅም የሚቀይር ኢንቨስትመንት በአካባቢው መኖሩን አመላክተዋል።
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የልማት ሥራዎችን ለመጎብኘት ድሬዳዋ ገብተዋል
May 17, 2026 268
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የልማት ሥራዎችን ለመጎብኘት ድሬዳዋ ገብተዋል፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው፤ የኢትዮጵያ መልክ፤ የፍቅር ርዕስ፣ የሥልጣኔና የዘመናዊነት ተምሳሌት ወደሆነችው ድሬዳዋ ገብተናል ብለዋል። የምድር ባቡር ፈርጥ፣ የንግድና የኢንዱስትሪ ማዕከል በሆነችው ድሬዳዋ ሲደርሱም ደማቅ አቀባበል ላደረጉላቸው ለከተማዋ ከፍተኛ አመራሮች፣ ለሀገር ሽማግሌዎች እና ለከተማው ህዝብ ላቅ ያለ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ በድሬዳዋ በሚኖራቸው ቆይታ በከተማዋ እየተሰሩ የሚገኙ ልዩ ልዩ የልማት ሥራዎችን እንደሚጎበኙም ገልጸዋል።
በሦስቱ ክልሎች ትብብር የሕዝቡን የጋራ ሰላምና ልማት ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተከናወኑ የሚገኙ ሥራዎች ውጤት እያመጡ ነው
May 17, 2026 219
አሶሳ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ እና በጋምቤላ ክልሎች ትብብር የሕዝቡን የጋራ ሰላምና ልማት ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተከናወኑ የሚገኙ ሥራዎች ውጤት እያመጡ መሆኑ ተገለጸ። በአሶሳ ከተማ የተገነባው የኦሮሚያ፣ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ እና የጋምቤላ ክልሎች የጋራ ሰላምና የልማት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ሕንጻ ተመርቋል። በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሐሰን፣ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ እና የጋምቤላ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) ተገኝተዋል። ክልሎቹ የሚጋሯቸውን አዋሳኝ አካባቢዎች የልማትና የሰላም ቀጠና ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትም የሕዝቡን ትስስር ወደ አዲስ ምዕራፍ እንዳደረሱት ተመልክቷል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሐሰን በወቅቱ እንደተናገሩት፤ ሦስቱ ክልሎች በጋራ እያከናወኗቸው የሚገኙት የሰላምና የልማት ሥራዎች በክልሎቹ መካከል ትብብር እንዲጎለብት አድርገዋል። የሕንጻው ግንባታ በክልሎቹ መካከል ያለውን ጠንካራ ግንኙነት በማስቀጠል ሁለንተናዊ ብልጽግናን የሚያረጋግጡ ሥራዎች ላይ በልዩ ትኩረት እየተሠራ መሆኑን ማረጋገጫ ነው ብለዋል። የሦስቱ ክልሎች የሰላምና የልማት ትብብር የመደመር አስተሳሰብን በተግባር የሚያሳይ እና የሕዝቦችን አብሮነት በማጠናከር ረገድ ጉልህ ሚና እንዳለውም ገልጸዋል። የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳ፤ በሦስቱ ክልሎች መካከል እየተገነባ ያለው የመሠረተ ልማት እና የሰላም ጥበቃ ስራ የሕዝብ ለሕዝብ ወዳጅነትን ይበልጥ እያጠናከረ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል። በተለይም የጋራ ምክር ቤቱ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ በሰላም እሴት ግንባታና በሕዝባዊ ተጠቃሚነት ላይ ያተኮሩ የመሠረተ ልማት ሥራዎች መከናወናቸውን የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ ይህም በሦስቱ ክልሎች መካከል ለሚኖረው ጠንካራ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር አስተማማኝ መሠረት መጣሉን ጠቅሰዋል። የጋምቤላ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የሦስቱ ክልሎች የጋራ ሰላምና ልማት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት በክልሎቹ መካከል ያለውን የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ከማጠናከር ባለፈ፣ በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድም ማኅበረሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ በርካታ ተግባራትን ማከናወኑን ገልጸዋል። በአሶሳ ከተማ የተገነባው የሦስቱ ክልሎች የጋራ ሰላምና ልማት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ባለ አራት ወለል ሕንጻ ሲሆን ግንባታው 300 ሚሊዮን ብር ወጪ እንደተደረገበትም ተገልጿል ።
የአዋሽ-ኮምቦልቻ-ሃራ ገበያ የባቡር መስመር ግንባታ ዳግም ሊጀመር ነው
May 17, 2026 243
ኮምቦልቻ ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦የአዋሽ-ኮምቦልቻ-ሃራ ገበያ የባቡር መስመር ግንባታን ዳግም ለማስጀመር የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን አስታወቀ። የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና የከተማ አመራሮች በኮምቦልቻ ጣቢያ በመገኘት የባቡር መስመሩን ግንባታ ዳግም ለማስጀመር የሚደረጉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን ተመልክተዋል። የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ምክትል ሥራ አስፈጻሚ ኢንጅነር ስለሽ ካሳ እንደገለጹት፤ ፕሮጀክቱ ማዕከላዊ ኢትዮጵያን ከሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል ጋር በማገናኘት ረገድ ከፍተኛ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ትስስር የመፍጠር አቅም አለው። የፕሮጀክቱ ግንባታ ተቋርጦ መቆየቱን አስታውሰው፣ አሁን ላይ የጥገናና የመልሶ ግንባታ ሥራውን በይፋ ለመጀመር የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በዚህ ወቅትም የሰው ኃይል የማሟላት፣ የማደሪያ ቤቶች ጥገና እና የመሠረተ ልማት ማመቻቸት ሥራዎች መጀመራቸውን ገልጸዋል። ሥራውን በፍጥነት ለማጠናቀቅ በአራት ቡድን ተከፋፍሎ ርብርብ እንደሚደረግ አመልክተው፣ አጠቃላይ ግንባታውን በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ ታቅዷል ነው ያሉት። የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ፕሮጀክቱ የንግድ ሥርዓቱን ለማሳለጥ፣ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና ቀጣናዊ ምጣኔ ሀብትን ለማነቃቃት ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። የፕሮጀክቱ ግንባታ መቋረጥ በሕብረተሰቡ ዘንድ ቅሬታና የመልካም አስተዳደር ችግር ፈጥሮ እንደነበር አስታውሰው፣ አሁን ላይ ዳግም ለመጀመር የተደረገው ዝግጅት የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። የክልሉ መንግስት ግንባታው በጥራትና በተያዘለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ተገቢውን ክትትልና ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮንን፣ "የፕሮጀክቱን ዳግም መጀመር የዞኑ ሕዝብ በጉጉት ሲጠብቀው የነበረ በመሆኑ፣ ለሥራው ስኬታማነት የዞኑ አስተዳደርና ሕዝብ ተገቢውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁና ቁርጠኛ ነው" ብለዋል። በተመሳሳይ የሰሜን ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አራጌ ይመር፣ "የባቡር ፕሮጀክቱ ዳግም መጀመር ለሕብረተሰቡ ትልቅ ተስፋ የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ የሚመረቱ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በቀላሉ ወደ መሃል አገርና ወደ ውጭ ገበያ ለመላክ፣ እንዲሁም ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በፍጥነትና በብዛት ለማጓጓዝ ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል" ብለዋል። "ኮምቦልቻ የኢንዱስትሪና የሎጅስቲክስ ከተማ በመሆኗ፣ የባቡር መስመሩ መነቃቃት ለከተማዋ ሁለንተናዊ ዕድገት ከፍተኛ ጥቅም አለው'' ያሉት ደግሞ የኮምቦልቻ ከተማ ከንቲባ አቶ መሀመድአሚን የሱፍ ናቸው። የአዋሽ-ኮምቦልቻ-ሃራ ገበያ የባቡር መስመር ፕሮጀክት አጠቃላይ ርዝመት ከ390 ኪሎ ሜትር በላይ ሲሆን፣ 51 ድልድዮች እና 12 ዋሻዎች እንዳሉት ተመልክቷል። በተጨማሪም ስምንት የኃይል መቆጣጠሪያ ጣቢያዎች እንዳሉትም ታውቋል።
በምግብ ራስን መቻል ዋነኛ አጀንዳችን ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 17, 2026 275
አዲስ አበበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፡- በምግብ ራስን መቻል ዋነኛ አጀንዳችን ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) ዛሬ ማለዳ ከአሊኮ ዳንጎቴ ጋር በመሆን በጎዴ እየተገነባ የሚገኘውን የዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካ ግንባታ የደረሰበትን ደረጃ ተመልክተዋል። ከጉብኝታቸው በኋላ በሰጡት ማብራሪያ፤ በምግብ ራስን ለመቻል መሬት ያስፈልጋል፣ ውኃ ያስፈልጋል፣ ሰው ያስፈልጋል እነዚህ ደግም አሉን ብለዋል። ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ ላይ እየሠራን ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ እነዚህን ካሟላን ለእኛ ብቻ ሳይሆን ለሌሎች የሚተርፍ ነገር ማድረግ ይቻላል ብለዋል። ሶማሌ ክልል ለልማት በጣም የተመቸ አካባቢ መሆኑን ጠቁመው፤ ያለውን መሬትና ውኃ ወደ መስኖ በማስገባት በሶማሌ ብቻ የሚለማው ለብዙ እንደሚተርፍ አመላክተዋል። ይህን ለማድረግም ሥራ፣ ሀብት እና ጊዜ እንደሚፈልግ አስረድተው፤ እነዚህን ካሳካን ብዙ ችግሮቻችንን የሚፈታ ጉዳይ ይሆናል ሲሉ አመላክተዋል።