ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በኦሮሚያ ክልል በበልግ እርሻ የታቀደውን ምርት ለማግኘት የሰብል እንክብካቤና ጥበቃ ላይ ትኩረት ተደርጓል
May 21, 2026 3
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በበልግ እርሻ የተዘሩ ሰብሎችን እንክብካቤና ጥበቃ በማድረግ የታቀደውን ምርት ለማግኘት ትኩረት መደረጉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ባሪሶ ፈይሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በበልግ አዝመራ ከለማው 1 ነጥብ 9 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ከ46 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዷል። ዘንድሮ የተከናወነው የበልግ እርሻ ስራ ከዕቅድ በላይ መፈጸሙን የገለጹት ኃላፊው፣ ለዚህ ስኬት ዋነኛው ምክንያት ያለውን አቅም አሟጦ መጠቀም በመቻሉ እንደሆነ አብራርተዋል። ለአርሶ አደሮቹ ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ግብዓትና የግብርና ቴክኖሎጂዎች መቅረባቸውን አስታውሰው በተለይ የዘንድሮው የበልግ አዝመራ የዝናብ ስርጭቱ የተሻለ በመሆኑ ሰብሉ በጥሩ ቁመና ላይ እንዳለ አመላክተዋል። በክልሉ በአሁኑ ወቅት በበልግ አዝመራው የታቀደውን ምርት ለማግኘት የሰብል ጥበቃና የእንክብካቤ ስራ ላይ ልዩ ትኩረት በመስጠት ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። ለዚህም ይረዳ ዘንድ የፀረ-አረምና የተባይ ኬሚካሎች ለአርሶ አደሮቹ በስፋት እየቀረቡ መሆኑን አስታውቀዋል። እንዲሁም አርሶ አደሮቹ ሰብሉን በቤተሰብ ደረጃና ከአካባቢያቸው ነዋሪዎች ጋር ሆነው በጋራ እየተንከባከቡ መሆኑን ገልጸዋል። በበልጉ የለማው ሰብል ላይ ጉዳት ሊያደርሱ የሚችሉ እንደ ግሪሳ ወፍ እና መሰል ተባዮችን አስቀድሞ ለመከላከል፣ በዘርፉ ባለሙያዎች አማካኝነት አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን ኃላፊው አክለው ገልጸዋል። ለዘንድሮው የበልግ እርሻ ስኬታማነት በየደረጃው የሚገኙ የግብርና ባለሙያዎችና አመራሮች የበኩላቸውን እየተወጡ መሆኑን የገለጹት ኃላፊው፤ የእርሻ መሬትን አስቀድሞ ከማዘጋጀት ጀምሮ ለአርሶ አደሩ ቀጣይነት ያለው ሙያዊ ድጋፍና ክትትል መደረጉንም ነው የጠቀሱት። በክልሉ የበልግ እርሻ በስፋት ከሚከናወንባቸው ዞኖች መካከል ምስራቅ ቦረና፣ ጉጂ፣ አርሲ፣ ምስራቅ እና ምዕራብ ሐረርጌ፣ ምስራቅ ባሌ እና ምስራቅ ሸዋ ዞኖች ሲሆኑ አጠቃላይ በክልሉ በ11 ዞኖች ውስጥ ነው ብለዋል።
ሀገር የተሟላ ክብርና ሉአላዊነት ሊኖራት የሚችለው ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት መውጣት ሲቻል ነው
May 21, 2026 51
ድሬዳዋ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገር የተሟላ ክብርና ሉአላዊነት ሊኖራት የሚችለው ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጅነት መውጣት ሲቻል ነው ሲሉ በድሬዳዋ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማእረግ የመንግስት ተጠሪ ኢብራሂም የሱፍ ገለጹ። "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና ግብርና ሚኒስቴር የተዘጋጀው የውይይት መድረክ በድሬዳዋ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት በድሬዳዋ አስተዳደር በምክትል ከንቲባ ማእረግ የመንግስት ተጠሪ ኢብራሂም የሱፍ፤ በለውጡ ዓመታት በመደመር እሳቤ የህዝብን ተጠቃሚነት እውን ያደረጉና ሀገርን ወደ ማንሰራራት የወሰዱ ስኬቶች ተመዘግበዋል ብለዋል።   በተለይም በስንዴ ልማት የላቀ ስኬት ስለመመዝግቡ አንስተው በተለያዩ የግብርና ኢንሸቲቮች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የመሸጋገር ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን አንስተዋል። ለውጡ እየተመራበት ያለው የመደመር እሳቤ የዜጎችን ተጠቃሚነት እንዲሁም የሀገርን እድገትና ማንሰራራት ለማሳለጥ ያስቻለ ስኬታማ አቅጣጫ መሆኑን ያሳየ መሆኑንም ተናግረዋል። በምግብ ራስን የመቻል ጥረት የሀገር ክብርና የትውልድ ዋስትና መሰረት መሆኑን በፅኑ በማመን መንግስት ለስኬቱ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ከተረጅነት የመውጣት ጉዳይ የዜጎችን ክብርና የሀገርን የወደፊት እጣ ፋንታ የሚወስን ወሳኝ ሀገራዊ አጀንዳ በመሆኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ ስለመሆኑ ተናግረዋል። በመሆኑም ሀገር የተሟላ ክብርና ሉአላዊነት ሊኖራት የሚችለው ከተረጅነት መውጣት ሲቻል መሆኑን አንስተው የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰይፈ ደርቤ፤ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመተባበር የሚካሄዱ መሰል መድረኮች ለሀገር የሚጠቅሙ ጥልቅ ሃሳቦች የሚነሱበት መሆኑን ገልጸዋል።   በመሆኑም እንደ ሀገር ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረጉ ጥረቶችንና የዜጎችን ብሩህ ተስፋ የሚያሳዩ የይዘት ስራዎችን በሚዲያ በስፋት ተደራሽ ማድረግ እንደሚገባ አንስተዋል። ኢትዮጵያ ከተረጂነት በመውጣት ምርታማነትን በማሳደግ እድገትና ማንሰራራቷ ቀጣይነት እንዲኖረው በስፋትና በጥልቀት የይዘት ስራዎችን ተደራሽ ማድረግ ይገባል ብለዋል። በመድረኩ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)፣ የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መሥተዳድር ሮዛ ዑመር፣ የፌዴራልና የክልል የመንግስት የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም ከድሬዳዋ አሥተዳደር፣ ከሶማሌ፣ ሐረሪ እና አፋር ክልሎች የተውጣጡ በርካታ አርሶ አደሮች ተገኝተዋል።
ከተረጂነት መላቀቅን የክብር ጉዳይ አድርጎ መትጋት ይገባል - ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)
May 21, 2026 73
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ ከተረጂነት መላቀቅ የሀገራዊ ሉዓላዊነትና የክብር ጉዳይ በመሆኑ ለዚሁ ስኬት በቅንጅት መትጋት እንደሚገባ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። “ከተረጂነት ወደ ምርታማነት” በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢፌዴሪ ግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የተዘጋጀ የፓናል ውይይት በድሬዳዋ ከተማ እየተካሄደ ነው።   ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) በዚሁ መድረክ ላይ ባቀረቡት የፓናል ውይይት መነሻ ጽሑፍ፤ በዕርዳታ እህል ትውልድን ማስቀጠል እንደማይቻል ገልፀዋል። የተሟላ ሉዓላዊነት ማለት፤ የብሔራዊ ደኅንነት ሉዓላዊነት፣ የምግብ ሉዓላዊነት፣ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት፣ የፖሊሲ ሉዓላዊነት፣ የባህልና የማንነት ሉዓላዊነት መሆኑንም አብራርተዋል። በዚህ መነሻም እንደሀገር ተረጂ ሆኖ፤ ልማትን፣ ፍላጎትን፣ ነጻነትን እንዲሁም ትውልድን ማስቀጠል የማይታሰብ ነው ብለዋል። ዕርዳታ ሰጪዎች ፍላጎታቸውንም እንድንፈፅም ማስገደዳቸው እንደማይቀር ታውቆ፤ ከተረጂነት በመውጣት አምራች መሆን የተሟላ ሉዓላዊነት ጉዳይ ነው ብለዋል። ተረጂነት ባርነትን ስለሚወልድ ማስቀረት ይገባናልም ነው ያሉት። ሊያጋጥሙ ለሚችሉ ሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች የራሳችንን ዐቅም መገንባት አለብን ሲሉም በአፅንኦት ገልፀዋል። የተሟላ ሀገራዊ ሉዓላዊነትን ከውስጥ ወደ ውጭ እያረጋገጡ መጓዝ ያስፈልጋልም ነው ያሉት።
የተሟላ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ተግባራት በይበልጥ ተጠናክረው ይቀጥላሉ
May 21, 2026 50
ድሬዳዋ፤ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦የተሟላ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ዘርፈብዙ ተግባራት በይበልጥ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በድሬዳዋ አሥተዳደር በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የመንግሥት ዋና ተጠሪ ኢብራሂም ዩሱፍ አስገነዘቡ። “ከተረጂነት ወደ ምርታማነት” በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር የተዘጋጀ የፓናል ውይይት በድሬዳዋ ከተማ እየተካሄደ ነው።   አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ በመድረኩ ላይ ባደረጉት ንግግር፥ ባለፉት የለውጥ አመታት ተጨባጭ ውጤት ያመጡ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተዋል። በመደመር ዕሳቤ ሁሉንም የሕብረተሰብ ክፍል ያሳተፈ ሥራ መከናወኑም አስታውቀዋል። በዚህም ሕዝቡን ያነቃቁ እና ተጠቃሚ ያደረጉ ስኬቶች መመዝገባቸውን ነው ያስረዱት። የተረጂነት አስተሳሰብን በማስወገድ ረገድ የሕዝቡ ሚና የላቀ መሆኑ ታምኖበት በተከናወኑ ተግባራት በድሬዳዋ አሥተዳደር ተረጂነትን በማስወገድ አምራችነትን የሚያሰፉ ሥራዎች ተሰርተዋል ብለዋል። በዚህም የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ የኑሮ ውድነትን ያረጋጉ ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቁመዋል። የተሟላ ሉዓላዊነት የሚገነባው የምግብ ዋስትናም ሲረጋገጥ መሆኑንም አጽንኦት ሰጥተዋል። ከምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥ ጋር በተያያዘ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልፀው፤ለዚህም የመድረኩ ሚና የጎላ መሆኑን ተናግረዋል።
በምዕራብ ወለጋ ዞን ከ279 ኪሎ ሜትር በላይ የገጠር መንገዶች ተጠግነዋል
May 21, 2026 53
ጊምቢ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦በምዕራብ ወለጋ ዞን ባለፉት አሥር ወራት ከ279 ኪሎ ሜትር በላይ የገጠር መንገዶች ተጠግነው ለአገልግሎት መብቃታቸውን የዞኑ መንገዶች ጥገና ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ አናቶሊ ቱፋ ለኢዜአ እንደተናገሩት፣ ባለፉት ዓመታት በዞኑ የገጠር መንገድ ተደራሽ ለማድረግ ሰፋፊ ሥራዎች ተከናውነዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ከመንገድ ተደራሽነቱ በተጨማሪ በተለያዩ ምክንያቶች የተጎዱ 329 ኪሎ ሜትር መንገዶችን ለመጠገን ታቅዶ ባለፉት አሥር ወራት ብቻ 279 ኪሎ ሜትር መንገድ ለመጠገን ተችሏል ብለዋል። የመንገድ ጥገና ሥራው በ12 የመንገድ መስመሮች ላይ የተከናወነ ሲሆን እነዚህም ወረዳን ከወረዳ እንዲሁም ወረዳን ከዞኑ ዋና ከተማ የሚያገናኙ መሆናቸውን አንስተዋል። ለጥገና ሥራው ከ56 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉን የገለጹት አቶ አናቶሊ፤ ጥገና ከተደረገላቸው የመንገድ መስመሮች መካከል ከጊምቢ-ጋምቤላ-ሖማ፣ ከአይራ-ቦንደዎ እና ከወራጂሩ-አባ ኤባ የሚወስዱ መንገዶች ይጠቀሳሉ ብለዋል። የመንገዶቹ መጠገን የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ከመፍታት ባለፈ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴን ማፋጠኑንና ለበርካታ ዜጎችም የሥራ ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል። በተለይም በዞኑ ቡና በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚመረት አስታውሰው፣ የመንገዱ መገንባት አርሶ አደሩ ቡናን ጨምሮ የሚያመርታቸውን የግብርና ምርቶች በቀላሉ ወደገበያ በማጓጓዝ ተጠቃሚነቱን ያሳድጋል ብለዋል። በዞኑ በአሁኑ ወቅት የሰፈነው ሰላም የመንገድ ጥገና ሥራውና መሰል የልማት ሥራዎችን ለማከናወን ጉልህ አስተዋጽኦ ማድረጉን ያነሱት ኃላፊው፤ የተበላሹ መንገዶች ተጠግነው ለትራንስፖርት ምቹ መደረጋቸው ለሌሎች የልማት ስራዎች መፋጠንም ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አመልክተዋል። የሖማ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አሸናፊ ጀማል እንደተናገሩት፤ ለመንገዶቹ የተደረገው ጥገና ከዚህ ቀደም በብልሽት ምክንያት ይደርስባቸው የነበረውን እንግልት አስቀርቷል። የህብረተሰቡን ማህበራዊ መስተጋብርና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ በማሳለጥ ይበልጥ ተጠቃሚ ለማድረግ ወሳኝ መሆኑንም አመልክተዋል። በአካባቢያቸው በስፋት የሚመረተውን ቡና እና ሌሎች የግብርና ምርቶችን ወደተለያዩ አካባቢዎች ገበያ አቅርበው በተሻለ ዋጋ ለመሸጥና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እንዳስቻላቸውም ተናግረዋል። አርሶ አደሩ የተጠገኑት መንገዶች ለረጅም ጊዜ አገልግሎት እንዲሰጡ አስፈላጊውን ጥበቃና እንክብካቤ እንደሚያደርጉም አክለዋል።
በክልሉ ባለፉት የለውጥ አመታት በብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ የታየው እመርታዊ ለውጥ ተጠናክሮ ይቀጥላል 
May 21, 2026 64
ጋምቤላ ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦በጋምቤላ ክልል ባለፉት የለውጥ አመታት በብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ የታየው እመርታዊ ለውጥ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን (ዶ/ር) ገለፁ። ''የጋምቤላ ክልል የለውጥ ብርሀን'' በሚል መሪ ሃሳብ የክልሉ መንግስት ከኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው በብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚ ላይ ያተኮረ የፓናል ውይይት ዛሬ በጋምቤላ ከተማ እየተካሄደ ነው።   ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በመድረኩ ላይ እንዳሉት፤ባለፉት የለውጥ አመታት መንግስት ለዘርፈ ብዙ የኢኮኖሚ ሴክተር ትኩረት ሰጥቶ ባከናወናቸው ተግባራት በርካታ ስኬቶች ተመዝግበዋል። በዚህም ክልሉ ያሉትን እምቅ የተፈጥሮ ፀጋዎችን በማልማት የህዝቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ አበረታች ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል። በቀጣይም ለኢኮኖሚ ዘርፉ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም የክልሉን የተፈጥሮ ሃብት ይበልጥ በማልማት እንደ ክልልም ሆነ እንደ ሀገር የተጀመረውን የብልጽግና ጉዞ ለማፋጠን በትጋት ይሰራል ብለዋል። በተለይም የግብርና ምርቶችን በማቀነባበር ለሚሰማሩ ኢንዱስትሪዎች ማበረታቻ ማቅረብ ላይ በትኩረት እንደሚሰራም አመልክተዋል። የከተሞችን እድገት ለማፋጠን መሰረት የሚጥሉ ተግባራትን እንደ ኮሪደር ልማትና የመሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎትን በማስፋት የመንግስትን አገልግሎት የማቀላጠፍ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። በቀጣይም የክልሉን የልማት እቅዶች በበለጠ ለማሳካት ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል። በፓናል ውይይቱ ላይ በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች፣ ምሁራንና ሌሎችም የሚመለከታቸው አካላት እየተሳተፉ ነው።
የአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታ የአካባቢውን ኢንቨስትመንት ያሳድጋል
May 21, 2026 73
ደብረ ማርቆስ ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ የደብረ ማርቆስ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ መጠናቀቅ የአካባቢውን የኢንቨስትመንት፣ የንግድና ቱሪዝም ልማት በማፋጠን የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድግ ነው ሲሉ የከተማ አስተዳደሩ የስራ ኃላፊዎች ገለጹ። የከተማ አስዳደሩ የኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ኀላፊ አቶ ተመስገን ተድላ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአውሮፕላን ማረፊያው የአካባቢውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት ለማፋጠን የላቀ ድርሻ አለው።   በተለይ ባለሃብቶች ያጋጥማቸው የነበረውን የትራንስፖርት ችግር በመቅረፍ ፕሮጀክቶቻቸውን በቅርበት ለመከታተልና ፣ ምርታማነታቸውን ለማሳደግ የሚያስችል እንደሆነም ተናግረዋል። በአካባቢው የሚመረቱ የኢንዱስትሪ ምርቶችን በፍጥነት ወደ ገበያ ከማቅረብ በተጨማሪም የአውሮፕላን ማረፊያው አዳዲስ ባለሃብቶችን ለመሳብም መልካም እድል ይዞ መምጣቱን አስረድተዋል። የከተማ አስተዳደሩ ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ተስፋዬ አእምሮ በበኩላቸው፤ የአውሮፕላን ማረፊያው የቱሪዝም ዘርፉን በከፍተኛ ሁኔታ የሚያነቃቃ መሆኑን ገልጸዋል።   በዋናነትም የአባይ በረሃን አቋርጦ በመምጣት በአካባቢው የሚገኙ ቅርሶችን ለመጎብኘት ያጋጥም የነበረውን ችግር በመቅረፍ የጎብኝዎችን ቁጥር ለመጨመር የሚያስችል ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የጮቄ ተራራን፣ ጥንታዊ ገዳማትና ሌሎች ቅርሶችን ለጎብኝዎች ክፍት ለማድረግም አሰጎብኝዎችን ከማደራጀት ጀምሮ ምቹ መስተንግዶ ለማቅረብ በተለየ ሁኔታ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የደብረ ማርቆስ ከተማ ንግድና ዘርፍ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ኢንጅነር ሙሉጌታ ይስማው በበኩላቸው፤ የአውሮፕላን ማረፊያው መገንባት የዘመናት የህዝብ ጥያቄን በመፍታት የንግድ እንቅስቃሴን ለማሳደግ የሚያስችል ነው ብለዋል።   አካባቢው በግብርናው ዘርፍ ትርፍ አምራች ከመሆኑም በላይ ያለውን የማዕድን ሃብት ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያግዝ መሆኑን አስረድተዋል። በተጨማሪም ከተማዋን የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማእከል ለማድረግ መልካም እድል ይዞ መምጣቱን ጠቁመው ይህም በአገልግሎት ዘርፉ የተሰማሩ ግለሰቦችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው ብለዋል ። በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ በግንባታ ላይ ያሉ ኢንዱስትሪዎችን ፈጥኖ በማጠናቀቅ አካባቢውን የንግድ ማእከል ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ከተረጂነት ወደ ምርታማነት በሚል መሪ ሐሳብ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ነው
May 21, 2026 156
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ ከተረጅነት ወደ ምርታማነት በሚል መሪ ሐሳብ የውይይት መድረክ በድሬዳዋ ከተማ እየተካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ይህ መድረክ በምርታማነት ጉዳይ ቁጭት ፈጥሮ የሚተጋ ማህበረሰብ መገንባትን ያለመ ነው። ከዚህ ቀደም በአዳማ እና በሃዋሳ በተዘጋጁ ተመሳሳይ መድረኮች የየክልሉን ተሞክሮ የዳሰሱ ውይይቶች ተካሂደዋል። የተለያዩ ክልሎችም ከተረጅነት ወደ ምርታማነትና ወደ ሉዓላዊ ክብር ለመጓዝ እያከናወኗቸው ያሉ ተግባራት ተዳሰዋል።   በዛሬው መድረክ ላይ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ፣ የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መሥተዳድር ሮዛ ዑመር፣ በድሬዳዋ ከተማ አሥተዳደር በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የመንግሥት ዋና ተጠሪ ኢብራሂም ዩሱፍ ተገኝተዋል። እንዲሁም የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴን (ዶ/ር) ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት ሥራ ኃላፊዎችም ተገኝተዋል። በተጨማሪም ከድሬዳዋ ከተማ አሥተዳደር፣ ከሶማሌ፣ ከሐረሪ እና ከአፋር ክልሎች የተውጣጡ አርሶ አደሮች በመድረኩ እየተሳፉ ይገኛሉ።
በብሄረሰብ አስተዳደሩ የተገነቡ መሰረተ ልማቶች ህዝቡን ተጠቃሚ እያደረጉ ነው
May 21, 2026 85
ሰቆጣ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ) ፦ በመንግስት የተገነቡ መሰረተ ልማቶች የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንዳስቻሉ የዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር የመንገድ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መምሪያ አስታወቀ። በብሄረሰብ አስተዳደሩ በ33 ሚሊየን ብር በላይ ወጭ የተገነቡ የኮንክሪትና የተንጠልጣይ ድልድዮች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ተደርገዋል ። በብሄረሰብ አስተዳደሩ በምክትል አስተዳዳሪ ማዕረግ የመንገድ ትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ መምሪያ ኃላፊ አቶ ፀጋው እሸቴ እንደገለፁት ፤ መንግስት የአካባቢውን ማህበረሰብ በመሰረተ ልማት በማስተሳሰር ስኬታማ ስራዎችን እያከናወነ ነው። በአሁኑ ወቅትም በ33 ሚሊዮን ብር ወጭ የተገነቡት በጋዝጊብላ ወረዳ የጎልሆ ወንዝ የኮንክሪት እንዲሁም የዝቋላ ወረዳ የጨዋ ተንጠልጣይ ድልድዮች መጠናቀቃቸውን አስረድተዋል። የእነዚህ መሰረተ ልማቶች መጠናቀቅ የማሕበረሰቡን ትስስር የሚያጎለብቱ መሆኑን የገለጹ ሲሆን በክረምት ወቅት በሰው፣ በእንስሳትና ሌሎች ንብረቶች ላይ ይደርስ የነበረውን የጎርፍ አደጋ የሚያስቀር መሆኑን ገልጸዋል። የጎልሆ ወንዝ የኮንክሪት ድልድይ ለስምንት ቀበሌዎች፤ የዝቋላ ወረዳ የጨዋ የተንጠልጣይ ድልድይ ደግሞ ለአራት ቀበሌዎች ክረምት ከበጋ አገልግሎት መስጠት የሚችሉ መሆኑን አንስተዋል። በተጨማሪም በፌደራል መንግስት ወጭ እየተገነባ የሚገኘው የሰቆጣ -ላሊበላ-ጋሸና የአስፋልት መንገድ ግንባታ መንግስት ለመንገድ መሰረተ ልማት ዘርፍ የሰጠውን ትኩረት የሚያመላክት ነው ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪም የጤና፣ የትምህርት፣ የኤሌክትሪክ፣ የንጹህ መጠጥ ውሃና ሌሎች የልማት ፕሮጀክቶችን በመገንባት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ እንደሆኑም አስረድተዋል። በአስተዳደሩ የጋዝጊብላ ወረዳ የመስቀሎ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ሞላ ማሞ እንዳሉት፤ የጎልሆ ወንዝ ድልድይ ግንባታ ተጠናቆ ለአገልግሎት መብቃቱ ለአካባቢው ማሕበረሰብ እፎይታን የሰጠ ነው። የድልድዩ መገንባት የክረምት ወቅት የሚከሰተውን የውሃ ሙላት በማስቀረት በተለይ የግብርና ምርቶችን ለማጓጓዝና ለገበያ ለማቅረብ እንዲሁም የኢንዱስትሪ ምርቶችን ወደ አካባቢው ለማስገባት እንደሚያስችልም ነው የተናገሩት።
በመዲናዋ የተገነቡ ግዙፍ ሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን ሕይወት እያሻሻሉ ነው
May 20, 2026 392
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ የተገነቡ ግዙፍ ሰው ተኮር የልማት ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን ሕይወት እያሻሻሉ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ የተለያዩ አካባቢዎች የተገነቡ የመኖሪያ ቤቶች፣ ሱቆችና የህጻናት መጫወቻ ፓርኮችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።   ከንቲባዋ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ ፓስተር አካባቢ የተገነባ ባለአምስት ወለል የመኖሪያ ቤት ህንጻን ዝቅተኛ ገቢ ላላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች አስረክበዋል። እንዲሁም በክፍለ ከተማው 40/60 ብርጭቆ ኮንደሚኒየም አካባቢ የተገነቡ ሁለገብ የህዝብ መዝናኛ ፓርክን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት፤ አዲስ አበባ ከስም በዘለለ በተግባር ውብ እና አበባ እየሆነች ትገኛለች ብለዋል። በከተማዋ የተገነቡ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ተመራጭ ከተማ እንድትሆን እንዳስቻሏት ገልጸዋል።   የከተማዋ ልማት ከዜጎች ህይወት መለወጥ እና መዘመን ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያለው መሆኑን አመላክተዋል። በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶች የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ፣ ምቹ የመኖሪያና የመዝናኛ አማራጭ የሚፈጥሩ እና የቱሪስት መስህብ መሆን የሚችሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። ነዋሪዎች የተገነቡትን ውብ የልማት ፕሮጀክቶች በአግባቡ በመጠበቅና በመንከባከብ ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የልማት ፕሮጀክቱ ተጠቃሚዎች በበኩላቸው፤ የተገነቡ የመኖሪያ ቤቶች፣ የህፃናት መጫወቻ ፓርኮች ወደ ዘመናዊና ምቹ አኗኗር የሚያሸጋግሩ ናቸው ብለዋል።
ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉ ስምምነቶች የአየር መንገዱን ዓለም አቀፍ ተደራሽነትና ገቢ ለማስፋት ጉልህ ሚና  ይጫወታሉ
May 20, 2026 191
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉ የአየር አገልግሎት ስምምነቶች የአየር መንገዱን ዓለም አቀፍ ተደራሽነትና ገቢ በላቀ ደረጃ ለማሳደግ ጉልህ ሚና እንዳላቸው የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ከተለያዩ ሀገራት ጋር በተደረጉ የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ የአስረጂዎች መድረክ አካሂዷል።   የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ባንግላዲሽ፣ አንጎላ፣ ኢስዋቲኒና ሴራሊዮን በሚያደርጋቸው በረራዎች የተፈረሙ የሁለትዮሽ የአየር አገልግሎት ስምምነት እንዲሁም በኢትዮጵያና ቬትናም መካከል የዲፕሎማቲክ ወይም ኦፊሻል አገልግሎት ፓስፖርት ለያዙ ሰዎች ቪዛን ለማስቀረት የተፈረመው ስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ በዝርዝር ውይይት ተደርጓል። የቋሚ ኮሚቴው አባላትና የምክር ቤቱ የህግ ማእከል በስምምነቶቹ ፋይዳ፣ የበረራ ደህንነት መጠበቅ፣ በኢሚግሬሽን ቁጥጥር፣ የአየር መንገዶች ገንዘብ የመታገድ ችግር፣ የአየር መንገዶች የመሬት ላይ አገልግሎቶች ጋር የተያያዙ አስተያየቶችና ጥያቄዎችን አንስተዋል። ከሀገራቱ ጋር የተደረገው ስምምነት ከኢትዮጵያ ህገ-መንግስት፣ ከሌሎች ህጎች እንዲሁም ሀገሪቱ ካፀደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎች ጋር እንዳይጋጭ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ዲማ ነጎ (ዶ/ር)፥ ረቂቅ አዋጆቹን የሀገራትን ሉዓላዊነት ባከበረ መልኩ የሀገሪቱን ደህንነት በማስጠበቅና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን በማጠናከር በተለያዩ አማራጮች ሀገሪቱን ተጠቃሚ ለማድረግ ማዳበር እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። ስምምነቶቹ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚሰጠውን አገልግሎት ተወዳዳሪነት ለማላቅና የሀገሪቱን ጥቅም በማስጠበቅ ረገድ ከተለያዩ ህጎችና ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ጋር የተጣጣመ መሆኑን ደግሞ የውይይቱ ተሳታፊዎች አስረድተዋል።   በኢትዮጵያ አየር መንገድ ዓለም አቀፍ ግንኙነት ተጠባባቂ ዳይሬክተር ጳውሎስ ኃይሌ፤ ከሀገራቱ ጋር የተደረጉ ስምምነቶች የአቪዬሽን ደህንነት፣ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ብሔራዊ ጥቅምን መሰረት ያደረጉ ናቸው ብለዋል። ስምምነቶቹ ለቱሪዝም፣ ንግድና ኢንዱስትሪዎች እድገት ጠቀሜታቸው ከፍ ያለ መሆኑን አንስተዋል። የአየር መንገዶች ገንዘብ የመታገድ ችግር ከባለድርሻ አካላት ጋር በዲፕሎማቲክ መንገድ እየተፈታ መሆኑን ገልጸዋል። አየር መንገዶች በተለያዩ ሀገራት የሚጠቀሟቸው የመሬት ላይ አገልግሎቶች የአየር መንገዶች አገልግሎት ብቃት ማሳያ መሆኑንና ከዓለም አቀፍ ስታንዳርዶች ጋር በተጣጣመ መልኩ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን የኢኮኖሚና ሬጉሌሽን ዳይሬክተር ናርዶስ በድሉ፤ ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የአየር መንገዱን ተደራሽነትና የትራፊክ መብቶችን የሚያሳድጉ እንዲሁም ተደራራቢ ቀረጥና ወጪን ለመቀነስ የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዓለም አቀፍ ህግ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል ይበቃል ግዛው፤ ከቬትናም ጋር የዲፕሎማቲክ ወይም ኦፊሻል አገልግሎት ፓስፖርት ለያዙ ሰዎች ቪዛን ለማስቀረት የተፈረመው ስምምነት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነትና የመወሰን ነጻነት የጠበቀ ነው ብለዋል።
በዞኑ የመሰረተ ልማት ተቋማት ግንባታን ከማስፋፋት ጎን ለጎን አገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመን ትኩረት ተደርጓል
May 20, 2026 318
መቱ ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በኢሉባቦር ዞን የመሰረተ ልማት ተቋማት ግንባታን ከማስፋፋት ጎን ለጎን የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ማሻሻል ትኩረት መደረጉን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በኢሉባቦር ዞን በበጀት ዓመቱ የተገነቡ 831 የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶችን ለአገልግሎት ክፍት የማድረግ መርሃ ግብር በሀሉ ወረዳ ተጀምሯል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ አስተዳደሩ ለሕብረተሰቡ ተጠቃሚነት የሚሰራ መሆኑን በተጨባጭ ስራዎች እያሳየ ነው። በዞኑ በትልቅ በጀት የሚሰሩ ትላልቅ የልማት ፕሮጀክቶችን በብዛትና በጥራት ለአገልግሎት በማብቃት ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉንም ተናግረዋል። በዚህም ዓመት በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የሕብረተሰቡን ጥያቄዎች የሚመልሱ፤ የአገልግሎት አሰጣጥ ቅሬታዎችን የሚፈቱ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተገንብተው ለአገልግሎት ክፍት መደረግ መጀመራቸውን ገልጸዋል። ከመሰረተ ልማት ተቋማት ግንባታ ጎን ለጎን የአገልግሎት አሰጣጥን ለማዘመንና ማሻሻል የተጀመሩ ስራዎች የሚጠናከሩ መሆኑን አስረድተዋል። ለምረቃ የበቁት ፕሮጀክቶችም የአስተዳደር ሕንጻዎች፣ ድልድዮች፣ የጤና ተቋማት፣ መንገዶች፣ የሶላር ኃይል ማመንጫ፣ የመጠጥ ውሃና የመስኖ ግድብ ፕሮጀክቶች መሆናቸውን ገልጸዋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ነመራ ቡሊ፣ በክልሉ በበጀት ዓመቱ የበርካታ ፕሮጀክቶች ግንባታ መካሄዱን አስታውሰዋል። ፕሮጀክቶቹ የልማትና የአገልግሎት ተደራሽነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የሀሉ ወረዳ ነዋሪዎች ለአገልግሎት እየበቁ የሚገኙ ፕሮጀክቶች በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ያለውን አቅም የሚያሳድጉ፤ የሕብረተሰቡንም ማሕበራዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። የአስተዳደር ሕንጻው ብዙ ሴክተር መስሪያ ቤቶችን በአንድ ሕንጻ ውስጥ የሚሰበስብ እንደመሆኑ አገልግሎት ለማግኘት የሚጠይቀውን ድካም የሚቀንስ መሆኑን ተናግረዋል።
ክልሉን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ የህዝቡን አቅም አቀናጅቶ መጠቀም ይገባል
May 20, 2026 255
ጋቼኖ ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልልን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ የህዝቡን አቅም አቀናጅቶ መጠቀም እንደሚገባ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ በወላይታ ዞን ዳሞት ጋሌ፣ ዳሞት ፑላሳ ወረዳዎች እና ሻንቶ ከተማ የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በምረቃው ላይ እንደገለጹት፤ ክልሉን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ የህዝቡን አቅም አቀናጅቶ መጠቀም ይገባል። የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ የተጀመረው ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል። ዛሬ በወላይታ ዞን በዳሞት ጋሌና በዳሞት ፑላሳ ወረዳዎች እንዲሁም በሻንቶ ከተማ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች የዚሁ አካል መሆናቸውን አንስተዋል። በበጀት ዓመቱ ባለፉት 9 ወራት 275 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ተገንብቶ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ትራንስፖርት እና መንገድ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ተወልደ ተስፋዬ ናቸው።   ዛሬ የተመረቀው የ15 ኪሎ ሜትር መንገድ በሻንቶ ከተማ፣ በዳሞት ፑላሳና በዳሞት ጋሌ ወረዳዎች የሚገኙ ቀበሌያትን የሚያገናኝ ነው ብለዋል፡፡ የሀርቶ ቆንጦላ ጫራቄ ተንጠልጣይ ድልድይ ደግሞ የዳሞት ጋሌና የዱጉና ፋንጎ ወረዳዎች ከ22 ሺህ በላይ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ እንደሚያደርግም አስረድተዋል። የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ በበኩላቸው፤ በዞኑ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ለአገልግሎት ክፍት በመደረጋቸው የህዝቡ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል።   ለአብነትም የማህበረሰብ መድኃኒት ቤት ግንባታ ህዝቡ በቅርበትና በተመጣጣኝ ዋጋ መድኃኒት እንዲያገኝ ማገዙን ጠቁመዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ በመንገድና ድልድይ ማጣት ሁለቱ ወረዳዎች ተለያይተው እንደቆዩ ተናግረዋል። አሁን መንግስት ችግሩ እንዲፈታ በማድረጉ የጤና አገልግሎት ለማግኘትም ሆነ በቀላሉ ወደ ገበያ ሄዶ ለመገበያየት እንደቻሉም ገልጸዋል፡፡   ከዚህ ቀደም መድኃኒት ለመግዛት ወደ ተለያዩ አካባቢዎች ርቀው ይጓዙ እንደነበርም ተናግረዋል። መድኃኒት ቤት በአቅራቢያቸው በመገንባቱ መድኃኒት በተመጣጣኝ ዋጋ እና በቅርበት ማግኘት በመቻላቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ የመንግስት ስራ ኃላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በክልሉ ለህብረተሰቡ የዘመናት ጥያቄ ምላሽ የሚሰጡ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት እየበቁ ነው-ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ
May 20, 2026 116
ሰመራ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦በአፋር ክልል ለህብረተሰቡ የዘመናት ጥያቄ ምላሽ የሚሰጡ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት እየበቁ መሆናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ ተናገሩ። ገቢ ረሱና ኸሪ ረሱ ዞኖችን እንዲሁም ወረዳዎችን ለማገናኘት የሚያስችሉ የጠጠር መንገዶችና ድልድይ በዛሬው ዕለት ተመርቋል። በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እንዳሉት፤ መንግስት ለህብረተሰቡ ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ምላሽ እየሰጠ ይገኛል።   ''ዛሬ ያስመርቅናቸው መንገዶችና ድልድይ ለረጅም ዘመናት በመንገድ ዕጦት ምክንያት ለተለያዩ ወጪዎች ተዳርጎ የቆየውን ህብረተሰብ በቅርብ ለማገናኘት የተቻለበት ነው'' ብለዋል። ይህ መንገድ ህብረተሰቡ ሲያነሳው የነበረውን ጥያቄ መመለስ የተቻለበት እና የህብረተሰቡ ተጠቃሚነት የተረጋገጠበት መሆኑን ገልፀው መሰል ስራዎችም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ ይህ እንዲሳካ ያደረገውን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር እንዲሁም የአካባቢውን ማህበረሰብ ለመንገዱ መጠናቀቅ ላደረገው ተሳትፎ አመስግነዋል።   የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ መንግስት ለህብረተሰቡ ተጠቃሚነት በትኩረት እየሰራ ይገኛል። ''የአርብቶ አደር አካባቢዎችን የልማት ማዕከል ለማድረግ የመንገድ ልማት አስፈላጊ መሆኑን ተረድተን ውጤታማ ስራዎች እያከናወንን እንገኛለን" ብለዋል። አርብቶ አደሩ ማህበረሰብ ከዚህ በበለጠ ተጠቃሚነቱ እንዲጨምር በትብብር የሚሰሩ ተግባራት የሚጠናከሩ መሆኑንም አክለዋል። በዛሬው ዕለት ለተመረቁት የጠጠር መንገዶችና ድልድይ ስራ 433 ሚሊዮን ብር በመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስቴር የቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አማካኝነት ወጪ የተደረገባቸው መሆኑ ተመላክቷል።
የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ እየተከናወነ ያለው ተግባር ይጠናከራል-እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
May 20, 2026 108
ግንቦት ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ ከለውጡ ወዲህ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ እየተከናወነ ያለው ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) አስታወቁ። የክልሉ እና የዞኑ ከፍተኛ አመራሮች በጉራጌ ዞን ከምሁር አክሊል ወረዳ ነዋሪዎች ጋር ህዝባዊ ውይይት አካሄደዋል።   በወቅቱም የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)፤ የክልሉ መንግስት ለህዝቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ እየሰጠ መሆኑን አንስተዋል። ለተነሱ የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ማህበረሰቡን ባሳተፈ አግባብ ምላሽ እንደሚሰጥም ርዕሰ መስተዳድሩ አመልክተዋል። የወረዳውን የመስህብ ስፍራዎች እና ቅርሶች በአግባቡ በማልማትና በማስተዋወቅ የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንዲሁም የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ለማስፋፋት ከባለሃብቶች ጋር በመቀናጀት እንደሚሰራም ገልጸዋል።   የምሁር ኢየሱስ ገዳም እና በዙሪያው ያሉ ቅርሶችን ለማልማት የተጀመሩ ስራዎችን ማጠናከር ከሁሉም እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። ባለሀብቶች በገዳሙ ዙሪያ የእንግዶች ማረፊያ በመገንባት ለዘርፉ እድገት አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱም ጥሪ አቅርበዋል። የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳደሪ አቶ ላጫ ጋሩማ በበኩላቸው በአካባቢው፤ ያለውን ፀጋና ሀብት በመጠቀም የህብረተሰቡን ኑሮ በማሻሻል ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ እየተከናወነ ያለው ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡   ሰፋፊ ኢንቨስትመንቶችን በመሳብ ለወጣቶች የስራ እድል ፈጠራን የሚያሰፉ ኢንዱስትሪዎች ትኩረት እንደተሰጣቸው አመልክተዋል። የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ ብስራት ገብሩ በበኩላቸው ከለውጡ ወዲህ የአካባቢን ጸጋ በማልማት የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል።   በወረዳው የህዝብ ጥያቄዎችን ለመፍታት በንፁህ መጠጥ ውሃ፣ በጤና ዘርፍ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በውይይት መደረኩ ላይ የተሳተፉ ከፍተኛ የክልሉና የዞኑ አመራሮች በዞኑ ምሁር አክሊል ወረዳ የሚገኘውን ታሪካዊው የምሁር እየሱስ ገዳምን ጎብኝተዋል።
በክልሉ በለውጡ ዓመታት የህዝብን የልማት ጥያቄ መሰረት ያደረጉ የተለያዩ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል 
May 20, 2026 100
ወንሾ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል በለውጡ ዓመታት የህዝብን የልማት ጥያቄ መሰረት ያደረጉ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ስራዎች መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ በማዕከላዊ ሲዳማ ዞን ወንሾ ወረዳ የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶችን ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል።   በምረቃው ላይ ርዕሰ መስተዳድሩ እንደገለጹት፣ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በክልሉ የህዝብን የልማት ጥያቄ መሰረት ያደረጉ ዘርፈ ብዙ የመሰረተ ልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። በዚህም ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ተጨባጭ ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቅሰው፣ በልማት ሥራዎቹ የህብረተሰቡ የተቀናጀ ተሳትፎ ጉልህ መሆኑን ተናግረዋል።   ዛሬ የተመረቁ የልማት ፕሮጀክቶች የክልሉ መንግስትና በየደረጃው ያሉ መዋቅሮች በቅንጅት ያስመዘገቡት ውጤት ነው ብለዋል። የልማት ፕሮጀክቶቹ የአገልግሎት አሰጣጥን በማሳለጥ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች የሚፈቱ መሆናቸውንም አስታውቀዋል። የወንሾ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ወልዴ ዩምራ በበኩላቸው፤ በወረዳው የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸውና ህዝቡም የተሳተፉባቸው ናቸው ብለዋል።   ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ከበቁ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶቹ መካከል ቅድመ መደበኛ ትምህርት ቤት፣ የወረዳ አስተዳደር ሕንጻ እና ሌሎች አገልግሎት የሚያሳልጡ የመንግስት ተቋማት እንደሚገኙበትም አመልክተዋል። የአካባቢው ህብረተሰብ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎችን በሂደት የመመለስ አቅም እያደገ መምጣቱን ገልጸው፣ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የአካባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ ሽታዬ እሳቱ፤ የለውጡ መንግስት ህብረተሰቡን በማስተባበር ባከናወናቸው የልማት ፕሮጀክቶች ህዝቡ ተጠቃሚነቱ እየተረጋገጠ መጥቷል። ዛሬ የተመረቁ ፕሮጀክቶችም አገልግሎትን የሚያሳልጡና የወረዳውን እድገት የሚያፋጥኑ ናቸው ብለዋል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደ፣ የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አብርሃም ማርሻሎ እንዲሁም ሌሎች የክልሉና የፌደራል መንግስት የሥራ ሃላፊዎችና የህብረተሰብ ክፍል ተወካዮች ተገኝተዋል።
ከተረጂነት ወጥተን በጀመርነው የገቢ ማስገኛ ሥራ ተጠቃሚ ሆነናል-አርሶ አደሮች
May 20, 2026 96
ሀዋሳ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ከምግብ ዋስትና ፕሮግራም ተረጂነት ወጥተው በጀመሩት የገቢ ማስገኛ ሥራ ተጠቃሚ ከመሆን ባለፈ ለሌሎችም እንደተረፉ አርሶ አደሮች ገለጹ። ግብርና ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋር በመተባበር "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ በሃዋሳ ባዘጋጀው መድረክ ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ አርሶ አደሮች እንዳሉት፤ በገቢ ማስገኛ ሥራ ላይ መሰማራታቸው ተጠቃሚ አድርጓቸዋል። ከዚህ ቀደም በምግብ ዋስትና መርሀግብር ታቅፈው በሚያገኙት አነስተኛ ገቢ ህይወታቸውን ይመሩ እንደነበር አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የሥራ ዘርፎች በመሰማራት ውጤታማ ከመሆን ባለፈ ለሌሎች መትረፍ እንደቻሉ ተናግረዋል። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስልጤ ዞን ስልጢ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ሙዲ ሀሰን እንዳሉት፤ ለዓመታት በፕሮግራሙ ታቅፈው በሚያገኙት አነስተኛ ገቢ ሕይወታቸውን ሲመሩ ቆይተዋል። በአካባቢያችን 65 ነዋሪዎች በመርሀግብሩ ድጋፍ ሲደረግልን ቆይተናል ያሉት አርሶ አደሩ፣ ከእነዚህ ውስጥ15ቱ በማህበር ተደራጅተው በንብ ማነብ እና በቅመማ ቅመም ልማት ሥራ መሰማራታቸውን ገልጸዋል። የንብ ማነብ ሥራውን በ25 ዘመናዊና ባህላዊ ቀፎ ታግዘው እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸው፣ በአንድ ተኩል ሄክታር ማሳ ላይም ሮዝመሪ በማልማት 300 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። በስልጤ ዞን ሁልባረግ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ካይሻ ኤርጌቾ፤ አካል ጉዳተኛ በመሆናቸው ለዓመታት በፕሮግራሙ በተደረገላቸው ድጋፍ ህይወታቸውን ሲመሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። በምግብ ዋስትና ፕሮግራም ያገኙትን ገንዘብ በመቆጠብ በጀመሩት የሱቅ እና አነስተኛ ግብርና ሥራ ገቢያቸውን በማሳደግ ከእርዳታ ሙሉ በሙሉ መውጣታቸውን ተናግረዋል። በሀላባ ዞን የሲምቢጣ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ገረመው መሀመድ፤ በቀበሌያቸው በተከሰተ የጎርፍ አደጋ ምክንያት ለዓመታት ከቀዬያቸው በመፈናቀል ለተረጂነት ተዳርገው እንደነበር አስታውሰዋል። በተደረገላቸው ድጋፍ ታግዘው በተለያዩ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሥራ መሰማራታቸውን ገልጸው፣ በዚህም ከተረጂነት ወጥተው በተለያየ አካባቢ መኖሪያ ቤቶችን በመገንባት ሀብት ማፍራታቸውን ጠቅሰዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጌዴኦ ዞን ኮቾሬ ወረዳ ነዋሪው ወጣት አርሶ አደር ታሪኩ ታደሰ በበኩሉ እንዳለው፣ ቀደም ሲል ምንም አይነት ገቢ ስላልነበረው በምግብ ዋስትና ፕሮግራም ሰርቶ በሚያገኘው አነስተኛ ገቢ ይተዳደር ነበር። በአሁኑ ወቅት በቡና እና በሥራ ሥር ተክሎች ልማት ተሰማርቶ ገቢውን በማሳደግ 2 ሚሊዮን ብር ሀብት ማፍራቱን ተናግሯል። በእዚህም ከእርዳታ ተላቆ ከራሱ ባለፈ በአቅራቢያው አቅመ ደካማ ቤተሰብ እያገዘ መሆኑንም ገልጿል። ከሲዳማ ዞን ሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ቱላ ቀበሌ የነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ዴቢቴ ናሮ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በመርሀግብሩ ያገኙትን ገንዘብ በመቆጠብ በጀመሩት የዶሮና ፍየል እርባታ ሥራ ከእርዳታ ተላቅቀዋል። በአሁኑ ወቅትም ያረቧቸውን ፍየሎች ለሌሎች በመስጠት ተጠቃሚ እንዲሆኑ እያገዙ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በኦሮሚያ ክልል በመኸር አዝመራ እስካሁን 6 ነጥብ 7 ሚሊየን ሄክታር የመሬት ዝግጅት ተደርጓል
May 20, 2026 199
ጅማ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በመኸር አዝመራ ለማልማት ከታቀደው መሬት እስካሁን 6 ነጥብ 7 ሚሊየን ሄክታር የመሬት ዝግጅት መደረጉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በዛሬው ዕለት የክልሉ ግብርና ቢሮ አመራሮች እና የጅማ ዞን የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በዞኑ ቦተር ጦላይ ወረዳ ለመኸር አዝመራ እርሻ የተዘጋጀ መሬትን በበቆሎ ዘር የመሸፈን ሥራ ተጀምሯል።   የቢሮው ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ በወቅቱ እንዳሉት፤ በክልሉ በዘንድሮው የመኸር አዝመራ 11 ነጥብ 1 ሚሊየን ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። በእስካሁኑ ሂደትም በመኸር አዝመራ ለማልማት ከታቀደው አጠቃላይ መሬት 6 ነጥብ 7 ሚሊየን ሄክታር የሚሆነው መሬት ተዘጋጅቷል ብለዋል።   ዘንድሮ የግብርና ግብዓቶች ለአርሶ አደሩ ቀደም ብለው እየቀረቡ በመሆናቸው በመኸር የተሻለ ውጤት እንደሚገኝ ተስፋ ተጥሏል ነው ያሉት። በክልሉ ግብርናን በሜካናይዜሽን ለማስፋፋት ባለፉት ዓመታት በቴክኖሎጂ የታገዘ ሥራ ሲሠራ መቆየቱን አስታውሰው፣ በዚህ ዓመት ብቻ 1 ሺህ 200 ትራክተሮች ለክልሉ አርሶ አደሮች መድረሳቸውን ገልጸዋል። በዚህ ወቅትም አጠቃላይ በክልሉ ከ11 ሺህ በላይ ትራክተሮች የግብርና ሥራውን በማቀላጠፍ ላይ ይገኛሉ ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪም ለዘንድሮ እርሻ ለአርሶ አደሩ ለማቅረብ ከታቀደው 10 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ 7 ሚሊየኑ ወደ ክልሉ የገባ ሲሆን፣ 3 ሚሊየን የሚሆነው ተሰራጭቷል ብለዋል። የጅማ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ዩሱፍ ሻሮ በዞኑ ለአርሶ አደሮች ቀደም ብሎ የግብርና ግብዓቶች እንዲቀርቡ መደረጉን ተናግረው፣ በዘንድሮው የመኸር እርሻ ከ 883 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዷል ብለዋል።   አጠቃላይ ከሚለማው መሬት ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ዘር የሚለማ መሆኑንም ጠቅሰዋል። የቦቶር ጦላይ ወረዳ አርሶ አደር ከበደ ታየ በ7 ሄክታር መሬት ላይ በቆሎ የማልማት ሥራ መጀመራቸውን ገልጸው፣ በኩታ ገጠም ማረሳቸው ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል።   አርሶ አደሩ ዘንድሮ በቂ የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ በማግኘታቸው ብዙ ምርት እንደሚጠብቁ ተናግረዋል። ሌላኛው አርሶ አደር ኡመር ቃሲም ከዚህ ቀደም በኩታገጠም በማልማት ከአንድ ሄክታር 75 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን ተናግረው በትራክተር ታግዘው በማረስ መሬታቸውን በዘር የመሸፈን ስራ መጀመራቸውን ገልፀዋል። በዘንድሮ እርሻ ለአርሶ አደሮች አስፈላጊ ሙያዊ እገዛ እየተደረገ መሆኑም ተመላክቷል።
ከተሞችን በማዘመን የእድገት ምንጭ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
May 20, 2026 104
ደብረ ብርሃን፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የሚገኙ ከተሞችን በማዘመን ለእድገት መሰረት እንዲሆኑ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሐመድ (ዶ/ር ) ገለጹ፡፡ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በደብረ ብርሃን ከተማ እየተከናወኑ ያሉ የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማ ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሐመድ (ዶ/ር ) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ መንግስት ከተሞችን በማዘመን ለኢንቨስትመንት ፣ ለቱሪዝምና ለኑሮ ምቹ እንዲሆኑ ያከናወናቸው ተግባራት ውጤት እየተመዘገበባቸው ነው።   በከተሞች ተገንብተው የተጠናቀቁና በመገንባት ላይ ያሉ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ለምጣኔ ሃብት እድገት መሰረት እየጣሉ መሆኑንም አረጋግጠዋል። በደብረ ብርሃን ከተማ በመገንባት ላይ የሚገኙ የኮሪደር ልማት፣ የአስፋልት መንገድ፣ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ግንባታና ሌሎች የመሰረተ ልማት ስራዎች ለዚህ ማሳያ ናቸው ብለዋል።   የደብረ ብርሃን ከተማን ለኢንዱስትሪ፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ተመራጭ እንድትሆን ለማድረግም የመሰረተ ልማት ግንባታ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት በበኩላቸው፤ ከተማዋ ለአምራች ኢንዱስትሪ ያላትን ተመራጭነት በመጠቀም የማምረት አቅምን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል።   በዛሬው እለት የተጎበኙትም የሶስት ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት፣ ከሁለት ነጥብ ሰባት ኪሎ ሜትር በላይ የአስፋልት መንገድን ጨምሮ የሶስት ኪሎ ሜትር የድንጋይ ንጣፍ መንገዶች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም 56 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ተገንብቶ ለአገልግሎት መብቃቱን ጠቁመው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ግንባታን በማጠናቀቅ የኔትወርክ ዝርጋታ እየተከናወነ እንደሚገኝም አስረድተዋል። የልማት ፕሮጀክቶቹም በከተማ አስተዳደሩና በነዋሪዎች የጋራ ትብብር እየተገነቡ የሚገኙ መሆናቸውን አስገንዝበዋል።
ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ ለማቅረብ የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል
May 20, 2026 107
ቃሉ፤ ግንቦት 12/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ ለማቅረብ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለፁ። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ በደቡብ ወሎ ዞን ቃሉ ወረዳ በ365 ሚሊዮን ብር የተገነባውን ዲርማ ወንዝ መስኖ ፕሮጀክት ዛሬ መርቀዋል።   በፕሮጀክቱ ምረቃ ላይ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በክልሉ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው። በተለይም ግብርናውን በሜካናይዜሽን፣ በቴክኖሎጂና በአዳዲስ አሰራር በማዘመን የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ የሚቀርብ ምርት ለማምረት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የገፀ ምድርና የከርሰ ምድር ውሃ በስፋት እንደሚገኝ ጠቅሰው፣ ይሄን የውሃ ሀብት ለመስኖ ልማት በማዋል ዓመቱን ሙሉ የማምረት ሥራው ይጠናከራል ብለዋል። ለእዚህም በክልሉ በርካታ የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ ሥራ እየተከናወነ ነው ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በቃሉ ወረዳ ዛሬ የተመረቀው ፕሮጀክትም ለእዚህ አንዱ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል። ፕሮጀክቱ በደቡብ ወሎ ዞን የቃሉ ወረዳ እና በኦሮሞ ብሔረሰብ ዞን የደዋጨፋ ወረዳን በጋራ የልማት ተጠቃሚ የሚያደርግ በመሆኑ ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ፋይዳው የጎላ ነው ሲሉም አክለዋል። የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የመስኖ መሰረት ልማቶችን በማስፋፋት አርሶ አደሩ ከዝናብ ጠባቂነት ተላቆ በመስኖ ጭምር በዓመት እስከ ሦስት ጊዜ በማምረቱ ውጤት እያስገኘ ነው።   በቃሉ ወረዳ በ365 ሚሊዮን ብር ተገንብቶ ዛሬ የተመረቀው የመስኖ ፕሮጀክት ከ290 ሄክታር በላይ መሬት በመስኖ ለማልማት የሚያስችልና ከ490 በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን አስታውቀዋል። ግንባታው በሰባት ወራት ጊዜ ውስጥ መጠናቀቁ የመንግስትን ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ ጀምሮ የመፈጸም ብቃት ያሳያል ብለዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮንን፤ በዞኑ የሚገነቡ በርካታ የመስኖ ፕሮጀክቶች ምርታማነትን በማሳደግ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል።   ዛሬ የተመረቀው የመስኖ ፕሮጀክት አርሶ አደሩ በዓመት ሦስት ጊዜ በማምረት ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ የሚያስችለው መሆኑን የገለጹት ደግሞ የቃሉ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሙህዲን አህመድ ናቸው። በምረቃው ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም