ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የደረጃ ‹‹ለ›› ግብር ከፋዮች እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ በኦንላይን ክፍያ መፈጸም ይጠበቅባቸዋል
Aug 5, 2026 117
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29/2018 (ኢዜአ) ፦የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮ መልዕክት የደረሳቸው የደረጃ ‹‹ለ›› ግብር ከፋዮች እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ በኦንላይን ክፍያቸውን በመፈጸም የዜግነት ግዴታቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቀረበ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ቢሮ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ሰውነት አየለ በሰጡት መግለጫ፣ቢሮው የግብር ስርዓቱን በማዘመን እና ፍትሃዊ አሰባሰብን በመዘርጋት ገቢን በጥራት እየሰበሰበ ይገኛል ብለዋል። ከተማ አስተዳደሩ ከሚሰበስበው ገቢ 72 በመቶውን ለዘላቂ ልማት፣ ለሰው ተኮር ፕሮጀክቶች እና ለኮሪደር ልማት በማዋል የመዲናዋን ገጽታና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት እያጎለበተ ይገኛልም ብለዋል። በከተማዋ በተለያዩ የንግድ ዘርፎች የተሰማሩ ከ456 ሺህ በላይ የደረጃ «ለ» ግብር ከፋዮች አዲስ በተሻሻለው የገቢ ግብር አዋጅ መሰረት ግዴታቸውን መወጣት እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝበዋል። ከደረጃ ‹‹ለ›› ግብር ከፋዮች በዘንድሮ በጀት ዓመት 9.2 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ መታቀዱን ገልጸዋል። መረጃቸው ለተሟላላቸው ግብር ከፋዮች የግብር ውሳኔ በስልክ የጽሁፍ መልዕክት የተላከ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፣ አብዛኛዎቹ ግብራቸውን በወቅቱ መክፈላቸውን አንስተዋል። እስከ ሐምሌ 25 ቀን 2018 ዓ.ም መልዕክት የደረሳቸው ግብር ከፋዮች እስከ ሐምሌ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ በኦንላይን በመክፈል ከቅጣት እና ወለድ ራሳቸውን መጠበቅ ይኖርባቸዋል ብለዋል። በተለያዩ ምክንያቶች መልዕክት ያልደረሳቸው ወይም ከሐምሌ 25 በኋላ የደረሳቸው ግብር ከፋዮች መልዕክቱ ከተላከላቸው ጊዜ ጀምሮ እስከ ነሐሴ 20 ቀን 2018 ዓ.ም ባሉት ቀናት ውስጥ ያለ ቅጣት ግብራቸውን መክፈል እንደሚችሉ አስታውቀዋል።
የባህር በር የዚህ ትውልድ ብሔራዊ አጀንዳ ነው
Aug 5, 2026 99
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29/2018 (ኢዜአ)፦ የባህር በር የዚህ ትውልድ ብሔራዊ አጀንዳ መሆኑን የማህበራዊ ሳይንስ ምሁር ብርሀኑ ሌንጂሶ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያ በታሪክም ሆነ ህጋዊ መሰረትን በካደ ሁኔታ ያጣችው የባህር በር ኢኮኖሚያዊ ዕድገቷን እንደጎዳው ምሁራን ያስረዳሉ። ኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤት እንድትሆንና ብሔራዊ ጥቅምን ማስከበር ላይ የተሄደበትን ርቀት አስመልክቶ ኢዜአ ከማህበራዊ ሳይንስ ምሁሩ ብርሀኑ ሌንጂሶ (ዶ/ር ) ጋር ቆይታ አድርጓል። ምሁሩ በቆይታቸው እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ታሪካዊ፣ ጂኦ-ፖለቲካዊና ህጋዊ መሰረትን የተከተለ ነው። በውጭ ኃይሎች ሴራና በሀገር ውስጥ በነበሩ ውስብስብ ችግሮች ምክንያት ሀገሪቱ ያጣችውን የባህር በር ባለቤትነት ለማስመለስ የጀመረችው ህጋዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ወቅታዊ መሆኑን ጠቁመዋል። ዓለም አቀፍ የባህር ህግ ወደብ የሌላቸው ሀገራት ወደ ባህር የመድረስና የመጠቀም መብታቸውን በግልፅ እውቅና ይሰጣል ብለዋል። ይህም ሀገራት ብሔራዊ ጥቅማቸውን ለማስከበርና የባህር በር ለማግኘት ለሚያደርጉት ዲፕሎማሲያዊና ህጋዊ ጥረት ትልቅ መሰረት ነው ሲሉ አክለዋል። ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟን በሴራ ብታጣም ዳግም የባህር በር ባለቤት ለመሆን የጀመረችው ጥረት የህግና የታሪክ መሰረት ያለው መሆኑን አስረድተዋል። የባህር በር ጥያቄው የኢትዮጵያን የንግድ ሚዛን ከማስጠበቅ ባሻገር፣ ለአፍሪካ ቀንድ ቀጣና የጋራ ተጠቃሚነትና አስተማማኝ ሰላም የላቀ አስተዋጽኦ እንዳለውም ብርሃኑ (ዶ/ር ) አክለዋል። ኢትዮጵያ አስተማማኝ የባህር በር ማግኘቷ ከጎረቤት ሀገራት ጋር የሚኖራትን የንግድና የኢኮኖሚ ትስስር በማሳደግ ቀጠናዊ ውህደትን ያፋጥናል ሲሉም ገልጸዋል። ብርሀኑ ሌንጂሶ (ዶ/ር) የባህር በር የትውልድ ብሔራዊ ህልውና ጉዳይ መሆኑንም ገልጸዋል። ለተግባራዊነቱም ዜጎች የፖለቲካም ሆነ ሌሎች አመለካከት ልዩነቶቻቸውን ወደ ጎን በመተው ለሀገር ብሔራዊ ጥቅም በጋራ መቆም አለባቸው ብለዋል። መንግስት በሰላማዊና በዲፕሎማሲያዊ መርህ የጀመረውን ጥረት ለማሳካት የሕዝብ ዲፕሎማሲ ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል ሲሉም አመልክተዋል። የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና የዘርፉ ምሁራን የባህር በር ለማግኘት የተጀመረውን ሀገራዊ ጥረት በምርምር፣ በታሪካዊና በህጋዊ ሰነዶች በማስደገፍ ሙያዊ ግዴታቸውን እንዲወጡ መክረዋል። የኢትዮጵያን ዘላቂ ጥቅም ለማስከበርና የባህር በር ባለቤትነትን እውን ለማድረግ አሁን የተጀመሩት ሁሉን አቀፍ ጥረቶች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ምሁሩ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በክልሉ የገበያ የክትትልና ቁጥጥር ስራዎች በማጠናከር የኑሮ ጫናን ለማቃለል ትኩረት ተደርጓል
Aug 5, 2026 132
አዲስ አበባ፣ሐምሌ 29/2018 (ኢዜአ)፡-በክልሉ በተያዘው የበጀት ዓመት የገበያ የክትትልና ቁጥጥር ስራዎች በማጠናከር እንዲሁም የግብርናና ኢንዱስትሪ ምርቶች አቅርቦት እንዲሻሻል በማድረግ የኑሮ ጫናን ለማቃለል በትኩረት እንደሚሰራ የሐረሪ ክልል ንግድ ልማት ኤጀንሲ አስታወቀ። የሐረሪ ክልል ንግድ ልማት ኤጀንሲ ኃላፊ አቶ ሸሪፍ ሙሜ በበጀት አመቱ በሚከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት ላይ መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም በያዝነው የበጀት አመት በክልሉ የኑሮ ጫናን ለማቃለል የሚያስችሉ ስራዎች በተጠናከረ መልኩ ይከናወናሉ ብለዋል። በተለይም የገበያ የክትትልና ቁጥጥር ስራዎች በማጠናከር የግብርናና ኢንዱስትሪ ምርቶች አቅርቦት እንዲሻሻል የማድረግ ስራዎች የላቀ ትኩረት ይሰጣል ብለዋል። ሸማቹን ማህበረሰብ ለአላስፈላጊ ወጪና ለእንግልት የሚዳርጉ ሰው ሰራሽ የዋጋ ጭማሪዎች የሚያደርጉ ነገዴዎች ተጠያቂ እንዲሆኑ የማድረግ ስራ ይሰራል ነው ያሉት። የምርት አቅርቦትን በማሻሻል፣ የገበያ ሰንሰለት ማነቆዎችን በመፍታትና ህገ-ወጥ ንግድን የመቆጣጠር ስራዎችም ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እንደሚሰራ ጠቁመዋል። የቅዳሜና እሁድ ገበያን በማጠናከር የአትክልትና ፍራፍሬ ምርቶችና የኢንዱስትሪ ውጤቶችን በቀጥታ ለሸማቹ በማቅረብ የኑሮ ጫናን ለማቃለል እንደሚሰራ ተናግረዋል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን በመኸር እርሻ 546 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቷል
Aug 5, 2026 142
ገንዳውኃ፣ ሐምሌ29/2018 (ኢዜአ):- በምዕራብ ጎንደር ዞን በመኸር እርሻ546 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መልማቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በዞኑ ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ ሞገስ ጋሹ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በምርት ዘመኑ በዞኑ ከ529 ሺህ 650 ሄክታር በላይ መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። በተደረገው ከፍተኛ ርብርብም እስካሁን ባለው ሂደት ከእቅድ በላይ ከ546 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የተለያዩ ሰብሎችን ማልማት እንደተቻለ ተናግረዋል። ከዚሁ ውስጥ ከ98 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት በባለሀብቶች የለማ ሲሆን፣ ቀሪው ደግሞ በአርሶ አደሮች መሸፈኑን ገልጸዋል። አኩሪ አተር፣ ማሽላ፣ ሰሊጥ፣ ጥጥ፣ ማሾና ሌሎች ሰብሎች በብዛት የለሙ መሆናቸውንም አመልክተው፤ በምርት ዘመኑ ከለማው መሬት ከ12 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። የተጀመረው እምቅ የልማት እንቅስቃሴ እስከ ምርት ስብሰባ ድረስ ተገቢው ክትትልና ድጋፍ እንደሚደረግለት ጠቁመዋል። በዞኑ በእርሻ ኢንቨስትመንት ከተሰማሩ ባለሀብቶች መካከል አቶ አብርሃም ድንቁ እንዳሉት፤ በዘንድሮው ዓመት ግብዓት እና የባለሙያ ድጋፍን በወቅቱ በማግኘታቸው የልማት ሥራዎችን በስፋት ማከናወን አስችሏቸዋል። በዚህም 200 ሄክታር መሬት በጥጥ፣ ማሽላ፣ አኩሪ አተርና ሰሊጥ ማልማታቸውን አመልክተው፤ ሰብሉ በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ትራክተሮችንና ሌሎች የግብርና ሜካናይዜሽን መሣሪያዎችን በስፋት በመጠቀማቸው ያቀዱትን መሬት በፍጥነት በዘር ለመሸፈን እንደቻሉም አብራርተዋል። በመተማ ወረዳ በግብርና ሥራ የሚተዳደሩት አርሶ አደር ብርሃኑ ጌታሁን በበኩላቸው፤ በመኸር እርሻው 15 ሄክታር መሬታቸውን ሙሉ ለሙሉ ማልማታቸውን ገልጸዋል። "የዝናብ ወቅቱን ጠብቀን በኩታ ገጠም አሰራር ነው መሬታችንን ያረስነው" ያሉት አርሶ አደሩ፤ የዝናብ ሥርጭቱን መሠረት ያደረገ የተባይና አረም ቁጥጥር እያደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። አሁን የተዘራው ሰብል ተስፋ ሰጪ በመሆኑ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁም ገልጸዋል። በዞኑ ባለፈው የ2017/18 የምርት ዘመን 525 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቶ ከ10 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደተገኘ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በኦሮሚያ ክልል እስካሁን ድረስ ከ8 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ተሸፍኗል
Aug 5, 2026 264
አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 29/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በመኸር አርሻ እስካሁን ድረስ ከ8 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች መሸፈኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ዘመናዊ የግብርና አሰራሮችንና ቴክኖሎጂዎችን በስፋት በመጠቀም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በምርት ዘመኑ በክልሉ ከ11 ነጥብ 1 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከ380 ሚሊዮን 659 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም እስካሁን በተደረገ እንቅስቃሴ ከ10 ሚሊዮን 199 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ታርሶ ለዘር መዘጋጀቱን ጠቅሰው፣ ከዚህ ውስጥ ከ8 ሚሊዮን 259 ሺህ በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በኩታ ገጠም ለምቷል ብለዋል። በሰብል ልማቱ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ከመሬት ዝግጅት ጀምሮ አጠቃላይ የክህሎት ማሻሻያና የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠናዎች መሰጠቱንም አቶ ጌቱ ተናግረዋል። በተጨማሪም ለአርሶ አደሩ በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በግብርና ሥራው በዋናነት በቆሎ፣ ስንዴ፣ ገብስ፣ ማሽላ እና ሌሎች ዋና ዋና የሰብል ዓይነቶች እንዲሁም የተለያዩ የቅባት እህሎች በስፋት እየለሙ መሆኑን አስታውቀዋል። ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ለአርሶ አደሩ ግብአት በስፋት መቅረቡን የተናገሩት ኃላፊው፣ በምርት ዘመኑ ከ14 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለማቅረብ ታቅዶ፣ ከ9 ሚሊዮን 864 ሺህ ኩንታል በላይ የሚሆነው በክልሉ የኅብረት ሥራ ማኅበራትና ዩኒየኖች በኩል እንዲቀርብ መደረጉን ገልጸዋል። እስካሁን በተከናወኑ ተግባራትም ከ6 ሚሊዮን 787 ሺህ ኩንታል በላይ ለአርሶ አደሮች መከፋፈሉን አክለዋል። ከዚህም በተጨማሪ የግብርና ምርታማነትን በመጨመር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ከማሳደግ ባለፈ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከቀረበው 673ሺህ 368 ኩንታል ምርጥ ዘር ውስጥ 627ሺህ 953 ኩንታሉ ጥቅም ላይ ውሏል ብለዋል። በአርሶ አደሮች ማሳ ለምቶ የተዘጋጀ ምርጥ ዘርም መቅረቡን ሃላፊው አክለው ገልጸዋል።
በጉጂ ዞን በበልግ ወቅት የለማ ሰብል በኮምባይነር በመታገዝ እየተሰበሰበ ነው
Aug 5, 2026 153
አዶላ፤ ሐምሌ 29/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በበልግ ወቅት የለማ ሰብል በኮምባይነር በመታገዝ እየተሰበሰበ መሆኑ ተገለፀ። በዞኑ የበልግ ወቅት ዝናብ ከመጋቢት እስከ ሚያዝያ ስለሚጥል የእርሻና የዘር ሥራ የሚካሄድ ሲሆን፤ ምርት ደርሶ የሚሰበሰብበት ደግሞ እስከ ነሐሴ አጋማሽ እንደሚዘልቅ ይታወቃል። በጽሕፈት ቤቱ የሰብል ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ መንግሥቱ ሂርባዬ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፣ በዞኑ በበልግ ወቅት 301 ሺህ 956 ሄክታር መሬት ለምቷል። ከዚህ ውስጥም ከ240 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በክላስተር መልማቱን ጠቅሰው ከለማው መሬትም ከ7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ አስታውቀዋል። በአሁኑ ወቅት ወደ ዞኑ በገቡ ኮምባይነሮች እና በሰው ኃይል በመታገዝ ምርት የመሰብሰብ ሂደት እየተፋጠነ መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይ ሰብልን በኮምባይነር መሰብሰብ ጊዜንና ጉልበትን ከመቆጠብ ባለፈ፣ የምርት ጥራትን ለማስጠበቅና ብክነትን ለመከላከል የጎላ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል። እስካሁን በተከናወነው ሥራ ከ149 ሺህ 175 ሄክታር በላይ መሬት ላይ 2 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት መሰብሰብ መቻሉን ገልፀዋል። የደረሰው ሰብል አልፎ አልፎ በሚጥል ዝናብ እንዳይበላሽ በርብርብ እየተሰበሰበ እንደሚገኝ ገልፀው በልማቱም ከ129 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን አውስተዋል። በዞኑ አዶላ ሬዴ ወረዳ የቂልጡ ሶርሳ ቀበሌ አርሶ አደር ሹና ጎበና በሰጡት አስተያየት፣ በበልግ ወቅት በኩታ ገጠም የዘሩት የስንዴ ሰብል ምርታማ እንዳደረጋቸው ገልፀው ከአካባቢው አርሶ አደሮች ጋር በደቦ ሰብላቸውን እየሰበሰቡ መሆኑን አመልክተዋል። የተሻሻለ ቴክኖሎጂን መጠቀም እና ሰብልን በመስመርና በክላስተር በመዝራት ከጀመሩ ወዲህ ምርታማነታቸውን በማደጉ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስረድተዋል።
በሀረሪ ክልል ክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራን ለማጎልበት በትኩረት ይሰራል
Aug 4, 2026 311
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 28/2018(ኢዜአ) ፦ በሀረሪ ክልል ክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራን በማጎልበትና የስራ ፈላጊዎችን የስራ ባህል ማሳደግ ላይ በትኩረት እንደሚሰራ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የክልሉ የስራ እድል ፈጠራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ወይዘሮ ሮዛ ኡመር ገለጹ። የክልሉ የስራ እድል ፈጠራ ምክር ቤት የ2018 በጀት አመት የስራ እድል ፈጠራ አፈጻጸም ሪፖርት እና የ2019 በጀት አመት እቅድ ላይ ውይይት አካሂዷል። ሰብሳቢዋ በመድረኩ ላይ በክልሉ የስራ አጥነት ችግርን ለመፍታትና አዳዲስ ቋሚ የስራ እድሎች ለመፍጠር ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራን በማጎልበት እንዲሁም የስራ ፈላጊዎችን የስራ ባህልና ግንዛቤ ማስፋት ከቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ መካከል መሆኑንም ወይዘሮ ሮዛ ተናግረዋል። በተለይም ገበያ ላይ ተፈላጊ የሆኑ የክህሎት ስልጠናዎችን ከመስጠት ጀምሮ የዜጎችን የስራ ባህል በማሳደግ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ተጠቃሚነታቸውን በዘላቂነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራም ጠቁመዋል። በ2019 የበጀት አመት እቅድን ለማሳካት በሚከወኑ ስራዎች የሚገጥሙ ውስንነቶችን ለመቅረፍ በትኩረት መንቀሳቀስ እንደሚገባ ገልጸው የሚመለከታቸው አካላትም በቅንጅት መስራት እንደሚኖርባቸው አሳስበዋል። በዚህም በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች ለስራ እድል ፈጠራ ዘርፍ ከእቅድ ጀምሮ እስከ አፈጻጸሙ ድረስ ቅድሚያ በመስጠት በልዩ ትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ ወይዘሮ ሮዛ ተናግረዋል፡፡ የክልሉ የኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኢስማኢል ዩሱፍ ባቀረቡት ሪፖርት እንዳመላከቱት በስራ እድል ፈጠራና ስልጠና ዙሪያ ከልማት አጋር አካላት፣ ከመንግስትና ከግል ሴክተሮች ጋር በቅንጅት ሲሰራ ቆይቷል። በተጠናቀቀው የበጀት አመትም 11 ሺህ ቋሚ የስራ እድሎችን በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በአገልግሎትና በውጭ ሀገር ስራ ስምሪት በገጠርና በከተማ ለሚገኙ ዜጎች መመቻቸቱ ተገልጿል። በተፈጠረው የስራ እድልም በዋናነት ወጣቶች፣ ሴቶች፣ አካል ጉዳተኞች እና ከስደት ተመላሽ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የማኅበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ነው
Aug 4, 2026 292
ቡታጅራ ፤ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ስራዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ገለፀ። በቢሮው "አንድነት ለፅዳት፣ ትጋት ለአገልግሎት፣ ውሳኔ ለልማት" በሚል መሪ ሐሳብ የተዘጋጀ የሴክተሩ የምክክር መድረክ በቡታጅራ ከተማ ተካሄዷል። በወቅቱም የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ስንታየሁ ወልደሚካኤል እንዳሉት በክልሉ የማኅበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማት ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ነው። በዚህም ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸው በኮሪደር ልማትና የሚሰጡ አገልግሎቶችን በማዘመን ረገድ የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። የስልጤ ዞን ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን መምሪያ ኃላፊ አቶ አብዱልሰመድ አብደላ በበኩላቸው በዞኑ ዘመናዊና የተሳለጠ አገልግሎቶችን በመስጠት የተገልጋይ እርካታን ለማረጋገጥ የሚያስችል ስራ እየተሠራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የኮሪደር ልማት ሥራ ከተሞችን ምቹ፣ ፅዱና ተመራጭ ከማድረግ ባለፈ የገጠር ቀበሌዎች ለኑሮ የተመቹና የወደፊቱን የከተሞች ዕድገት ታሳቢ ባደረገ መልኩ እንዲለሙ እየተደረገ ነው ብለዋል። ለዚህም ስኬት በዞኑ በሚገኙ 3 ወረዳዎች የአርሶ አደሩን የአኗኗር ዘዬ የሚቀይሩ 24 ቤቶች መገንባታቸውንና በዕቅድ የተያዙትን ቀሪ ቤቶች ለማጠናቀቅ እየተሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በከተማው በመሬት ዘርፍ በሚሰጡ አገልግሎቶች የሚነሱ የማኅበረሰቡን ቅሬታዎች ለመፍታት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው ያሉት ደግሞ የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሽጉጤ ናቸው። በተለይም 45 የሚጠጉ የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶች በመሶብ የአንድ ማዕከል እንዲሰጡ መደረጉ ለውጥ እንዳመጣም ጠቁመዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮችና የዘርፉ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
በክልሉ የከተሞችን እድገትና የገጠር የልማት ሽግግር ዘላቂነት ታሳቢ ያደረገ ፕላን በማዘጋጀት እየተተገበረ ነው
Aug 4, 2026 294
ባህር ዳር፤ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የወቅቱን የከተሞችን እድገትና የገጠር የልማት ሽግግር ዘላቂነት ታሳቢ ያደረገ ፕላን በማዘጋጀት እየተተገበረ እንደሚገኝ የክልሉ ፕላን ኢንስቲትዩት ገለጸ። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ምትኩ ዓለማየሁ (ዶ/ር) ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳሉት፤ በክልሉ ከተሞችና የገጠር ቀበሌዎች መጪውን እድገትና የሕዝብ አኗኗር መሠረት ተደርጎ እየተሠራ ነው። ከተሞች ካላቸው ፈጣን እድገት ጋር ተያይዞ ዘላቂነት ያለው የመሠረተ ልማት ግንባታ፣ የመኖሪያ አካባቢዎች፣ ማህበራዊ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማትንና ሌሎችንም ሁኔታዎች ባሟላ መንገድ መጪውን ጊዜ ታሳቢ በማድረግ በፕላን እንዲመሩ እየተደረገ ይገኛል። እንዲሁም የገጠር ሽግግርን የተሳካ ለማድረግ የገጠር ቀበሌ ማዕከላት በፕላን ላይ መሠረት አድርገው እንዲቋቋሙ በቅንጅት እየተሠራ እንደሆነም አንስተዋል። በተለይም የኮሪደር ልማት ኢኒሼቲቭ፣ ከተሞችና የገጠር አካባቢዎች በዘላቂ ፕላን እንዲመሩ አስገዳጅ ከመሆኑም በላይ ለዘላቂ እድገት መልካም ሆኖ መገኘቱን ተናግረዋል። ኢንስቲትዩቱ በ2018 በጀት ዓመት ተቋማዊ ሪፎርም ከማድረግ ባሻገር ለአሠራር የሚያግዙ የሕግ ማሻሻያዎችን የማድረግ ሥራ ተሠርቷል ብለዋል። እንዲሁም 137 የተለያየ ዓይነት ፕላን በማዘጋጀት ወደ ትግበራ እንዲገባ መደረጉን ጠቅሰው፤ ከእነዚሁ ውስጥ 37 የሚሆኑት የገጠር ቀበሌ ማዕከላት ፕላኖች መሆናቸውን ገልጸዋል። በፕላን ዝግጅቱ ከ14 ሺህ በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ማሳተፍ መቻሉን ጠቅሰው፤ የፕላን ትግበራ፣ ክትትልና ቁጥጥር ሥራ መካሄዱንም አብራርተዋል። ኢንስቲትዩቱ በ2019 በጀት ዓመትም 187 የተለያየ ዓይነት ፕላን ለማዘጋጀት አቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን ጠቅሰዋል። የፕላን ዝግጅቱ የክልሉን የ25 ዓመት አሻጋሪ የልማትና የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ መሠረት በማድረግ እየተተገበረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ከሚዘጋጀው ፕላን ውስጥም 130 ያህሉ የገጠር ቀበሌ ማዕከላት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ይህም መንግሥት ለገጠር ሽግግር የሰጠውን ትኩረት መሠረት በማድረግ የሚሠራ ነው ብለዋል። የገጠር ማዕከላቱ የመኖሪያ አካባቢዎችን፣ መሠረተ ልማትን፣ የገበያ ቦታዎችን፣ ማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማትንና የአርሶ አደሩን የግብርና ሥራ በሚያሳልጥ አግባብ የሚሠሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። ተዘጋጅተው የሚቀርቡ ፕላኖች ወደ ትግበራ ሲገቡ በየደረጃው የሚገኝ አመራርና ባለሙያ ሕብረተሰቡን በማሳተፍ መተግበር እንዳለበትም ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል።
ታዋቂው ሲ ኤን ኤን ቴሌቪዥን ጣቢያ ስለ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ
Aug 4, 2026 474
ታዋቂው የሲኤንኤን የቴሌቪዥን ጣቢያ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ከኢትዮጵያ ባለፈ የቀጣናው ሀገራትን የኢነርጂ ተጠቃሚ ያደረገ ግዙፍ ፕሮጀክት መሆኑን በዘገባው አስቃኝቷል። ግድቡ በሚሊየኖች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያዊያን ብርሃን ያደረሰ መሆኑንም አመላክቷል። በሲኤንኤን ዘጋቢ የሆነችው ቪክቶሪያ ሩባዲሪ ባሰናዳችው ዘገባ÷ ወደ ጉባ በማቅናት የግድቡን እውነታ አስቃኝታለች። በዚህም በሺዎች የሚቆጠሩ በርካታ የምህንድስና ባለሙያዎች እና የግንባታ ባለሙያዎች ሸለቋማ የሆነውን አካባቢ ወደ አፍሪካ ግዙፍ ግድብ መቀየራቸውን ገልጻለች። ግድቡ የምህንድስና ልህቀት የታየበት ነውም ብላለች። ከ14 ዓመታት የግንባታ ቆይታ በኋላ ህዳሴ ግድብ እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር መስከረም 2025 መመረቁን ገልጻለች። ግድቡ በኢትዮጵያውያን ድጋፍ፣ የመንግስት ፋይናንስ፣ ቦንዶች እና የተለያዩ የሀገር ውስጥ የፋይናንስ አማራጮች በኢትዮጵያዊያን አቅም መገንባቱን ተናግራለች። ይህ ግዙፍ ግድብ ለሚሊዮኖች ኢትዮጵያውያውን ብርሃን የሚሰጥ ብቻ ሳይሆን በጎረቤት ሀገራትም የኤሌክትሪክ ሃይል አቅርቦት እንዲደርስ የሚያደርግ ነው። በዚህም ግድቡ ከኢትዮጵያ ባለፈ የቀጣናዊ ኃይል ትስስር ማእከል እንዲሁም የቱሪስት መዳረሻ በመሆን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው የጎላ መሆኑን ተናግራለች። ሲኤን ኤን በዘገባው ላይ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ክፍሌ ሆሮን በማቅረብ ኢትዮጵያ የታችኛውን ተፋሰስ ሀገራት በማይጎዳ መልኩ ግድቡን እየተጠቀመች መሆኑን አመላክቷል። ግብፅ በግድቡ ምክንያት የሚደርሳት ውሃ ቀንሷል በሚል የምታቀርበው ክስ መሰረተ ቢስ መሆኑንም ኢንጂነር ክፍሌ አስረድተዋል፡፡ አሁን ላይ በሕዳሴ ግድቡ የሚገኙ 13 ተርባይኖች በሚያመነጩት ሀይል 6 ሚሊየን ኢትዮጵያውያን የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ግድቡ ከኢትዮጵያ አልፎ ሱዳን፣ ጅቡቲ፣ ኬንያ እና ታንዛኒያ ሀይል ተደራሽ ማድረግ መቻሉን፣ በቀጣይ ደግሞ ለሶማሊያ እና ደቡብ ሱዳን ሀይል ለመሸጥ ዝግጅት መደረጉን አመላክተዋል፡፡ በተጨማሪም በሕዳሴ ግድቡ በተፈጠረው ንጋት ኃይቅ ላይ የተፈጠሩት ደሴቶች ለቱሪስት መስህብነት ትልቅ አቅም መሆናቸውን በማንሳት ፤ በቀጣይም ለቱሪስት መዳረሻነት የሚያገለግሉ መሰረተ ልማቶች እንደሚገነቡ ጠቁመዋል፡፡
በክልሉ ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት አምጥተዋል
Aug 4, 2026 294
ቡታጅራ ፤ ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ) ፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት ማምጣታቸውን የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ገለፀ። ቢሮው አንድነት ለፅዳት፣ ትጋት ለአገልግሎት፣ ውሳኔ ለልማት በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጀው የምክክር ጉባኤ በቡታጅራ ከተማ እየተካሄደ ነው። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የኢንዱስትሪ ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ሀላፊ አቶ ስንታየሁ ወልደሚካኤል በወቅቱ እንዳሉት፤ በ2018 በጀት ዓመት በክልሉ ከተሞችን በማህበረሰብ ተሳትፎ በማልማት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ማሳደግ ተችሏል። በክልሉ መንግስት ለከተሞች ልማት ከመደበው በጀት ባለፈ ህብረተሰቡ ከ2 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር በላይ ማዋጣቱን ተናግረዋል። በዚህም የውስጥ ለውስጥ አስፓልትን ጨምሮ የመንገድ፣ የውሃና ሌሎች መሰረተ ልማት ስራዎች ተደራሽነትን በማስፋት የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል። ከተሞችን ውብና ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ በክልሉ ሰባት ከተሞች በሁለት ምዕራፍ 165 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የክልሉን ከተሞች የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተጀመሩ ስራዎችን ለማጠናከርና የተስተዋሉ ጉድለቶችን ለማረም የምክክር መድረኩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት አመልክተዋል። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ደሱ አበጋዝ በበኩላቸው፤ በዞኑ በበጀት ዓመቱ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ በርካታ የልማት ስራዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት ስለመደረጋቸው ተናግረዋል። ከተሞችን ውብና ፅዱ ለነዋሪዎች ምቹ ለማድረግ በተጀመሩ ስራዎች በቡታጅራ ከተማ በመጀመሪያ ምዕራፍ እየተተገበረ ከሚገኘው 21 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ውስጥ 11 ነጥብ 26 ኪሎ ሜትር የሚሆነው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ስለመደረጉም ጠቅሰዋል። የከተማዋን የአገልግሎት አሰጣጥ በማዘመን የማህበረሰቡን እርካታ ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። በምክከር መድረኩ የክልል፣ የዞን፣ የልዩ ወረዳ፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና የዘርፉ ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው።
የግብርና ምርትና ምርታማነት እድገት የምግብ ሉአላዊነት እንዲረጋገጥ እያስቻለ ነው
Aug 4, 2026 354
ወልቂጤ፤ ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና ምርትና ምርታማነት እድገት የምግብ ሉአላዊነት እንዲረጋገጥ እያስቻለ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ከክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ጋር በመሆን በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ እንዲሁም በቀቤና ልዩ ወረዳ ኩታ ገጠም የበቆሎ እርሻዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በወቅቱ እንደተናገሩት፤ በክልሉ የግብርና ሜካናይዜሽንና የኩታ ገጠም እርሻ የግብርና ምርታማነት እንዲጨምር አድርጓል ። ለዚህም ለአርሶ አደሩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችንና የግብአት አቅርቦት ተደራሽነት ላይ በቅንጅት መሰራቱን ተናግረዋል፡፡ የግብርና ምርትና ምርታማነት እያደገ በመምጣቱም የምግብ ሉአላዊነት እየተረጋገጠ እንዲመጣ እያስቻለ መሆኑን አመልክተዋል። ይህም የአርሶ አደሩን ገቢ በማሳደግ የኢኮኖሚያዊ ሽግግርን ለማፋጠን የራሱን አቅም እየፈጠረ መሆኑን ጠቁመዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የግብርናና ገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር በበኩላቸው፤ በጉራጌ ዞን በአበሽጌ ወረዳ እንዲሁም በቀቤና ልዩ ወረዳ በበቆሎ ልማት የመጣው ለውጥ የአርሶ አደሩ የግብርና ሙያተኞችን ምክር የመከተል ውጤት ነው ብለዋል። ቢሮው ምርታማነትን ለማሳደግ የኩታ ገጠም አሰራር ተግባራዊ እንዲሆን ከመድረግ ባለፈ የምርት ብክነትን የሚቀንሱ የግብርና ቴክኖሎጂዎች ጥቅም ላይ እንዲውሉ ድጋፍ ማድረጉን ተናግረዋል። የዚሁ ማሳያ የሆነው የኩታ ገጠም የበቆሎ ልማትም ሰብሉን ለመንከባከብና ዘመናዊ አመራረትን ለመተግበር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። በዘርፉ የመጣውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል እንደሚሰራም አመላክተዋል።
በአማራ ክልል የፍራፍሬ ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳደገ ነው
Aug 4, 2026 255
ደሴ ፤ ሐምሌ 28/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል እየተካሄደ የሚገኘው የፍራፍሬ ልማት የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት እያሳደገ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ ገለፁ። የአማራ ክልል፣ የዞንና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች በቃሉ ወረዳ በክላስተር የለማ ፍራፍሬ ልማት ጎብኝተዋል። የቢሮ ኃላፊው አቶ ደረጀ ማንደፍሮ እንደገለፁት፣ ክልሉ ለፍራፍሬ ልማት ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ይገኛል። ባለፉት ሰባት ዓመታትም ቡናና አቮካዶን ጨምሮ ሌሎች የፍራፍሬ አይነቶች በመመረታቸው ከፍጆታ አልፎ ለውጭ ገበያ ጭምር ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል። በክልሉ በአሁኑ ወቅት አርሶ አደሩን በማደራጀት በኩታ ገጠም የፍራፍሬ ልማት እንዲሳተፍና ምርታማነቱን እንዲያሳድግ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም 37 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ከ26 ሚሊዮን በላይ የቡናና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች እየተተከሉ መሆኑን ገልጸዋል። በቃሉ ወረዳ በኩታ ገጠም የለማው የፍራፍሬ ችግኝም ተስፋ ሰጭና ለሌሎች አካባቢዎች ተሞክሮ የሚሆን ነው ብለዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው፣ ዞኑ ለፍራፍሬ ልማት ያለውን ምቹነት በመጠቀም የአርሶ አደሩን ገቢ ማሳደግና ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። አርሶ አደሩን በማደራጀት በኩታ ገጠም ማንጎ፣ ፓፓያ፣ ብርቱካን፣ አቮካዶና ሌሎች ፍራፍሬዎችን በማልማት ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። በዘንድሮው አረንጓዴ አሻራም ሶስት ሺህ 700 ሄክታር መሬት በፍራፍሬ ችግኝ እየተሸፈነ እንደሚገኝ ጠቁመው አሁን ላይ መስኖን በመጠቀም በበጋ ጭምር የፍራፍሬ ችግኞችን መትከል መቻሉን ተናግረዋል። አርሶ አደሩ የፍራፍሬን ጥቅም በተግባር በማየቱ በኩታ ገጠም እየተደራጀ ማልማት ጀምሯል ያሉት ደግሞ የቃሉ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሙህዲን አህመድ ናቸው። በዚህም በአጭር ጊዜ ምርት የሚሰጡና በሽታን የሚቋቋሙ ዝርያዎችም በመንግስት እየቀረቡላቸው ነው ብለዋል። በቃሉ ወረዳ የ033 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሙባረክ መሀመድ እንደገለጹት ፣ ፍራፍሬን በክላስተር ማልማት መቻላቸው ተጠቃሚ አድርጓቸዋል። ባለፉት ጥቂት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተከሉዋቸው የማንጎና ሙዝ ችግኞች ለገበያ በማቅረብ በዘንድሮ ዓመት ብቻ ከ70 ሺህ ብር በላይ ማግኘታቸውን ገልጸዋል። በዘንድሮው ክረምትም ተጨማሪ 200 የማንጎ ችግኞችን መትከላቸውን ተናግረዋል። በጉብኝቱ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች፣ የአማራ ክልል ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴዎችና አባላትን ጨምሮ ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ ነው
Aug 3, 2026 533
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ መምጣቱን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) ገለጹ። የዘንድሮው "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሃሳብ የሚካሄደው የ800 ሚሊዮን የአንድ ጀምበር የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ዛሬ ሐምሌ 27/2018 ዓ.ም ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በመላ ሀገሪቱ ተካሄዷል። የፕላንና ልማት ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት አመራርና ሠራተኞች በአንድ ጀምበር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በአዲስ አዳማ ፈጣን መንገድ ዳርቻ የአረንጓዴ ዐሻራቸውን አኑረዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን በመቋቋምና የአፈርና የውሃ ሀብት ጥበቃን በማጠናከር ዘርፈ ብዙ የኢኮኖሚ ፋይዳ እያስገኘ ነው። ይህም የኃይል ማመንጫ ግድቦችን ለደለል ተጋላጭነት ከመቀነስ ባለፈ የኤሌክትሪክ ኃይልን ዘላቂነትና የምግብ ዋስትናን የሚያጠናክር አቅም እየፈጠረ መሆኑን አብራርተዋል። በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርም የሚኒስቴሩና ተጠሪ ተቋማት አመራርና ሠራተኞች ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞችን መትከላቸውን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩም የኢትዮጵያን የአቮካዶና ሌሎች የፍራፍሬ ምርቶች ወጪ ንግድ ምርታማነትን በማሳደግ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለውጭ ምንዛሬ ግኝት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል። የዜጎችን የይቻላል መንፈስ በማጎልበትም ኢትዮጵያ በአፍሪካና በዓለም አቀፍ ደረጃ እውቅና እያተረፈች መሆኗን ገልጸዋል። የሕዝቡ ከፍተኛ ተሳትፎም አብሮነትና አንድነትን በማጠናከር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የሀገራዊ የልማት ባህል እንዲሆን እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና በማሳደግ የዜጎች የሀገራዊ ልማት ባህል እየሆነ መምጣቱንም አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ጀሚላ መሀመድ በበኩላቸው፤ በዛሬው ዕለት በሚኒስቴሩና ተጠሪ ተቋማቱ የተተከሉት የፍራፍሬ ችግኞች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ናቸው ብለዋል። ህብረተሰቡ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ለታቀደው ግብ ስኬት ችግኞችን በመትከልና በመንከባከብ የበኩሉን ሚና እንዲወጣም ጥሪ አቅርበዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ ነው
Aug 3, 2026 401
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ለኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ዕድገትና ለካርበን ልቀት መቀነስ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታዎች ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ሚኒስቴርና የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ከተጠሪ ተቋማቱ ጋር በመሆን በአንድ ጀምበር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር አሻራቸውን አኑረዋል፡፡ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ስለሺ ግርማ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ችግኝ መትከል ለቱሪዝም ዘርፍ ዕድገት መሠረት መጣል ነው፡፡ በዱር እንስሳት ጥበቃ ስፍራዎችና በብሔራዊ ፓርኮች ውስጥ ያለውን የደን ሽፋን እንዲጨምር በማድረግ በኩል ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡ መርሃ ግብሩ የዱር እንስሳትን ስደት ከመቀነስ ባሻገር የፓርኮችን የቱሪስት መስህብነት በከፍተኛ ደረጃ በማሳደግ ጎብኚዎች ከተፈጥሮ ጋር የሚገናኙበትን፣ ንጹህ አየርና አረንጓዴ አካባቢን የሚመርጡበትን የዘላቂ ቱሪዝም ዕድል ያሰፋል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የምታሳየው የተግባር ምላሽ ዓለም አቀፍ ገጽታዋን በበጎ በመቀየር በዘላቂና በአረንጓዴ ቱሪዝም አርአያ እንድትሆን ማስቻሉን ገልጸዋል፡፡ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሀሰን መሀመድ በበኩላቸው፤ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያውያንን አንድነት በተግባር ያሳየበት ታሪካዊ ክስተት ነው ብለዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመረው ይህ ንቅናቄ ኢትዮጵያን በአየር ንብረት ጥበቃ አርዓያ እና የዓለም አቀፍ የችግሮች መፍትሄ አካል ያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የካርበን ልቀትን መቀነስ ቀዳሚ ግቡ መሆኑን በማንሳት፤ አረንጓዴ ዐሻራ በአንድ በኩል የምድርን ጸጋ መጠበቅ በሌላ በኩል ደግሞ የአየር ብክለትን የመከላከል ሚና እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት የተተከሉ የቡና፣ አቮካዶ እና የፍራፍሬ ችግኞች ለቤተሰብ የገቢ ምንጭ፣ ለሀገር ደግሞ የውጭ ምንዛሬ መሳቢያ መሆን ጀምረዋል ብለዋል፡፡ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል፣ የበረሃማነት መስፋፋት በመግታትና እና ለውሃ እጥረት ምላሽ በመስጠት ለነገው ትውልድ የተሻለች ሀገር ማስረከብም እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እያነጸ ይገኛል
Aug 3, 2026 331
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ በጽኑ መሠረት ላይ እያነጸ እንደሚገኝ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። በአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ሀገራዊ ግብ ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በይፋ እየተካሄደ ይገኛል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር አመራሮች እና ሠራተኞች “ተስፋን እንትከል” በሚል መሪ ሐሳብ በቢሾፍቱ ፈጣን መንገድ ላይ ችግኞችን ተክለዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት ሚኒስትሩ አለሙ ስሜ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ መርሃ ግብሩ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከልና በሀገሪቱ የተዘረጋውን የአረንጓዴ ትራንስፖርት ስትራቴጂ ለማገዝ ከፍተኛ ሚና አለው። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር የአፈር መሸርሸርን ለመከላከል፣ የውሃ ሀብትን ለመጠበቅ እና ለተተኪው ትውልድ የሚተርፍ የተፈጥሮ ፀጋን ለማስረከብ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ሰባት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የተተከሉ ችግኞች የደን ሽፋን ከመጨመር ባሻገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረጉ ሥራዎች ላይ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙ አውስተዋል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በከተሞች አካባቢ ደንን ማስፋፋት የከተሞችን ሙቀት በመቀነስ ሰዎች በእግር ወይም በብስክሌት በቀላሉ እንዲንቀሳቀሱ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር አብራርተዋል። ኢትዮጵያ ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የምታደርገውን ሽግግር በዋናነት የምትደግፈው በኤሌክትሪክ ኃይል በመሆኑ፣ የአረንጓዴ አሻራ እንቅስቃሴ የዝናብ ዑደትንና የግድቦችን ደህንነት በመጠበቅ አስተማማኝ ንጹህ ኃይል እንዲኖር እንደሚያስችል ገልጸዋል፡፡ መርሃ-ግብሩ ሀገሪቱ የያዘችውን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ በጽኑ መሠረት ላይ የሚጥል መሆኑን አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍራኦል ጣፋ ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለችው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋምና ምርታማነትን ለማሳደግ ጉልህ ድርሻ እንዳለው ገልፀዋል። ባለሥልጣኑ ከዚህ ቀደም የተተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ የተሻለ የጽድቀት ምጣኔ እንዲኖር ሲሰራ መቆየቱንና ይህንን ተግባር አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሲቪል አቬሽን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ዮሐንስ አበራ በበኩላቸው ዓለም በካርበን ልቀት ምክንያት እየተፈተነች እንደምትገኝ ገልፀው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ይህንን ለመከላከል አይነተኛ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የፐብሊክ ሰርቪስ ትራንስፖርት ዋና ዳይሬክተር አስካለ ተክሌ በበኩላቸው፤ በትራንስፖርት ዘርፉ የበካይ ጋዝ ልቀትን ለመከላከል በመርሃ ግብሩ ተሳታፊ በመሆን ችግኝ መትከል ብቻ ሳይሆን ተከታትሎ የመንከባከብ ስራም እያከናወንን እንገኛለን ብለዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ ፅዱና ማራኪ ከተሞችን በመፍጠር ለነዋሪዎች ምቹ የከተሜነት ምህዳር እየገነባ ነው
Aug 3, 2026 333
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ፅዱና ማራኪ ከተሞችን በመፍጠር ለነዋሪዎች ምቹ የከተሜነት ምህዳር እየገነባ መሆኑን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ፡፡ "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሐሳብ የሚካሄደው የአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኝ ተከላ ሀገራዊ መርሃ ግብር ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በመላ ሀገሪቱ እየተካሄደ ይገኛል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማትም በዚሁ ሀገራዊ መርሃ ግብር በመሳተፍ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ አካሂደዋል። የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በዚሁ ወቅት፤ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የአብሮነትን መንፈስ በማጠናከር፣ ሀገረ መንግሥትን በመገንባትና የዜጎችን የኑሮ ደረጃ በማሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። መንግሥት የሕዝብን ተሳትፎ በማሳደግ የሚተከሉ ችግኞችን ከመትከል ባለፈ በአግባቡ በመንከባከብ እስከ ፍሬ እንዲደርሱ በትኩረት እየሠራ መሆኑንም ገልጸዋል። የከተማ ልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራምም የከተማ ግብርናን በማስፋፋት፣ የአካባቢ ጥበቃና ውበትን በማጎልበት፣ ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠርና የኑሮ ደረጃቸውን በማሻሻል ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ከተሞች የመኖሪያ ስፍራ ብቻ ሳይሆኑ የምርት ማዕከላት እንዲሆኑ ታስቦ የተነደፈው ፕሮግራም የተተከሉ ችግኞችን ከመንከባከብ ጀምሮ ለምርት እስኪደርሱ ድረስ ክትትል የሚደረግበት መሆኑንም አብራርተዋል። አረንጓዴ ልማቶች የዜጎችን ተጨማሪ ገቢ ከማሳደግ ባለፈ፣ ከተሞችን ምቹ፣ ንጹሕና አረንጓዴ በማድረግ ለቀጣይ ትውልድ ተስማሚ የኑሮ አካባቢ ለመፍጠር ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ አስረድተዋል።
በካፋ ዞን የሻይ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በይፋ ተጀመረ
Aug 3, 2026 288
ካፋ፤ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በካፋ ዞን የሻይ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በዛሬው ዕለት በይፋ ተጀመረ። የሻይ ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በካፋ ዞን ሺሾ እንዴ ወረዳ ዋና ቦላ ቀበሌ በዛሬው እለት ተከናውኗል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ፤ የሻይ ልማትን ለማስፋት የተያዘውን እቅድ መሰረት በማድረግ በዞኑ አራት ወረዳዎች ችግኝ የማዘጋጀት ስራ ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል። በመሆኑም በአራት የችግኝ ጣቢያዎች 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን የሻይ ችግኞች መዘጋጀታቸውን አንስተው የመትከል ስራው በዛሬው እለት በይፋ መጀመሩን ተናግረዋል። በዚሁ መሰረትም ከዛሬ ጀምሮ በቀጣዮቹ ተከታታይ 15 ቀናት በተዘጋጀው 110 ሄክታር መሬት ላይ የመትከል ስራው የሚከናወን መሆኑን ገልጸዋል። የሺሾ-እንዴ ወረዳ ግብርና አካባቢ ጥበቃና ሕብረት ስራ ልማት ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አዱኛ አለሙ፤ በበኩላቸው በወረዳው የአየር ንብረት ለውጥን ከመቋቋም በተጨማሪ ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬና የውጭ ምንዛሬን ለማያስገኙ ለቡናና ሻይ ችግኞች ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ከአረንጓዴ አሻራ ኢንሼቲቭ ጋር በማያያዝ የሻይ ችግኞችን በማዘጋጀት በዛሬው እለት በዋና ቦላ ቀበሌ ተከላ መጀመሩን ገልጸዋል። በወረዳው 43 ነጥብ 5 ሄክታር መሬት ለሻይ ልማት መዘጋጀቱን ጠቅሰው የችግኝ ተከላው ይቀጥላል ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ማስጀመሪያ ለይ የተገኙት የደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ባለሥልጣን ከፍተኛ ባለሙያ አቶ ካሳሁን ታዬ፤ በክልሉ በዘንድሮው ዓመት ለሻይ ልማት ልዩ ትኩረት በመስጠት የተሟላ ዝግጅት በማድረግ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል። በተያዘው እቅድ መሰረትም ዘንድሮ የሻይ ችግኝ ተከላ በብዛት የሚከናወን ይሆናል ብለዋል። ከዋና ቦላ ቀበሌ ነዋሪዎች መካከል አርሶ አደር ጌታቸው ወልደጊዮርጊስ እና አቶ ንጉሴ ገብረሚካኤል የልማት ስራው በብዙ መልኩ ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል።
ዛሬ የተከልናቸው የፍራፍሬ ችግኞች አማራጭ ገቢ የሚያስገኙልን ናቸው
Aug 3, 2026 256
አዋሽ መልካሳ፤ሐምሌ 27/2018 (ኢዜአ)፦በዛሬው ዕለት በአንድ ጀምበር በተካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃግብር የተተከሉት የፍራፍሬ ችግኞች፣ ከመደበኛው ግብርና ጎን ለጎን ለአርሶ አደሩ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እንደሚሆኑ በአዋሽ መልካሳ የመርሃግብሩ ተሳታፊዎች ገለጹ። በመርሃ ግብሩ ላይ ከተሳተፉት መካከል ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት አቶ ቱጂ አብዶ፣ የፍራፍሬ ችግኝ ተከላ ለትውልድ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። በተለይም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር እንደሚረዳ የጠቆሙት አቶ ቱጂ፣ ሥራው ለራሳችን፣ ለክልላችንም ሆነ ለሀገራችን የሚጠቅም ነው ሲሉ ገልጸዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርና የፍራፍሬ ችግኝ ተከላው ለነገው ትውልድ ስንቅ እንደሚሆን አንስተው፤ ችግኞቹን ከመትከል ባለፈ ተንከባክበው ለፍሬ እንደሚያበቋቸው ገልጸዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ አመለወርቅ አያሌው በበኩላቸው፣ ዛሬ የተከሉት ችግኝ ለነገው ትውልድ ተስፋ እንዲሆን በማሰብ መሆኑን ገልጸዋል። ወይዘሮ አመለወርቅ አክለውም በየዓመቱ መርሃ ግብሩ ላይ መሳተፋቸውን ጠቅሰው፣ባለፉት አራት ዓመታት በተካሄዱት የተከላ መርሃ ግብሮች በመሳተፍ የተተከሉትን ችግኞች በመንከባከብ ውጤታማ ማድረግ መቻላቸውንም ገልጸዋል። የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ሳይንሳዊ ይዘቱን ተከትሎ እንዲከናወን በተሰጠው ግንዛቤ መሠረት እየተገበሩ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ አቶ አብደላ ከድር ናቸው። ችግኞችን መትከል ብቻ ሳይሆን በዘላቂነት በመንከባከብ ለውጤት ማብቃት እንደሚገባ ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ መተላለፉንም ገልጸዋል። በተለይም የአቮካዶ፣ የማንጎ፣ የፓፓያ፣ የሎሚ፣ የብርቱካንና የዘይቱን ችግኞች በስፋት መተከላቸውን ገልጸው፤ ይህም አርሶ አደሩ ከመደበኛ የሰብል ልማት ጎን ለጎን ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኝ የሚያስችለው መሆኑን ተናግረዋል። ይህም በምግብ ራስን ለመቻልና ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት ቁልፍ አጋዥ መሆኑን አስረድተዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አለሙ ቂልጡ በበኩላቸው፣ በዘንድሮው የክረምት ወቅት ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞች በ100 ሄክታር መሬት ላይ በክላስተር መተከላቸውን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ የፍራፍሬ ችግኞች የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የኑሮ ውድነትን ለመቋቋምና የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ወሳኝ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በተጨማሪም ችግኞቹ የአርሶ አደሩን ሕይወት ለማሻሻልና ገቢውን ለማሳደግ የሚያስችሉ መሆናቸውን የጠቆሙት አቶ አለሙ፤ ይህም አርሶ አደሩ ገበያ ተኮር በሆኑ የግብርና ምርቶች ላይ በስፋት እንዲሰማራ በማድረግ ዘላቂ ለውጥ ለማምጣት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ የተሻለ ምርት የሚሰጡ የአቮካዶ፣ የሎሚና የብርቱካን ምርጥ ዘሮችን ከውጭ በማስገባት ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጋቸውን አክለው ገልጸዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ለምለሚቷን ኢትዮጵያ ለመጪው ትውልድ የምናስረክብበት ትልቅ ተስፋ ነው
Aug 3, 2026 302
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 27/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ለምለሚቷን ኢትዮጵያ ለመጪው ትውልድ የምናስረክብበት ታላቅ ተስፋ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ በአንድ ጀምበር 800 ሚሊዮን ችግኞችን የመትከል ሀገራዊ ግብ ከማለዳው 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በይፋ የተጀመረ ሲሆን፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ አሻራቸውን አሳርፈዋል። ከንቲባዋ በዚህ ወቅት ባደረጉት ንግግር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ለምለሚቷን ኢትዮጵያ ለመጪው ትውልድ የምናስረክብበት ትልቅ ተስፋ ነው ብለዋል። ዛሬ ለምለም ኢትዮጵያን ለመገንባት በእጆቻችን ዝቅ ብለን የምንትክልበት፣ በሐሳብ አንድ ሆነን በተግባር ሀገራችንን በአረንጓዴ የምናልብስበት መርሃ ግብር ነው ብለዋል፡፡ በዚህ መርሃ ግብር እየተከልን ያለነው ምግባችንን፣ ጥላችንን እና ውበታችንን ነው ያሉት ከንቲባዋ፤ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚመጡ ተግዳሮቶችን ለመከላከል ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው አብራርተዋል፡፡ በሀገራችን ባለፉት ሰባት ዓመታት 48 ቢሊዮን ችግኞች መተከላቸውን ያነሱት ከንቲባ አዳነች፤ ይህም በጋራ እና በትብብር የሰራነው የዘመናችን ታላቅ ውርስ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም በከተማ አስተዳደሩ የሚገኙ ሁሉም የማህበረሰብ ክፍሎች በጋራ በመሆን በተዘጋጁ ቦታዎች ላይ ችግኞችን እየተከሉ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ የተተከሉትን ችግኞች በአግባቡ መንከባከብና መከታተል እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡