ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ሀገራት በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ ፍትሃዊ ውክልና ሊኖራቸው ይገባል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 12, 2026 235
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ):- በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ ፍትሃዊና ተደማጭነታቸውን ያረጋገጠ ውክልና ሊኖራቸው እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። 18ኛው የብሪክስ ጉባኤ ዛሬ በህንድ ኒው ዴልሂ መካሄድ ጀምሯል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር የማዕድን ሀብት ለኢነርጂ ሽግግር፣ ለላቀ ማኑፋክቸሪንግ እና ለዲጂታል ኢኮኖሚ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። አፍሪካ የበርካታ ማዕድናት ሀብት ባለቤት መሆኗን ጠቅሰው፤ የብሪክስ አባል ሀገራት ደግሞ የካፒታል፣ የቴክኖሎጂ እና የገበያ አማራጭ እንዳላቸው አንስተዋል። እነዚህን ሀብቶች አቀናጅቶ ለመጠቀምና በጥሬ ሃብቱ ላይ እሴት ለመጨመር የብሪክስ ጥምረት ትልቅ እድልን የሚፈጥር መሆኑን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በማዕድናት፣ በታዳሽ ኢነርጂ እና እያደገ ያለውን የኢንዱስትሪ አቅሟን መሰረት ባደረገ መልኩ አጋርነቶችን ለመፍጠር ዝግጁ መሆኗን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ ለአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ትስስር ያላት አበርክቶ ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ አፍሪካን ከዓለም ጋር እያገናኘ እንደሚገኝ በማሳያነት ጠቅሰዋል። ለጎረቤት ሀገራት የምታቀርበው የኤሌክትሪክ ኃይል ለሀገራቱ ኢኮኖሚ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ አዲስ አበባ የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ መሆኗንም አንስተዋል። ኢትዮጵያ ብሪክስ እና የአፍሪካ ህብረት ያላቸው ትብብር ከአጀንዳ 2063 ጋር የተጣጣመ እንዲሆን ድጋፏን እንደምትሰጥም አመልክተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ስርዓት ጋር በተያያዘ ባነሱት ሀሳብ የኢኮኖሚ ሪፎርም ማድረጓን እና የውጭ ዕዳዋን ለማሸጋሸግ እየሰራች መሆኗን ገልጸዋል። በፈተና ውስጥ ለሚገኙ ኢኮኖሚዎች ጊዜ ውድ ሀብት መሆኑን ጠቅሰው፤ የዕዳ አከፋፈል ሂደት ፈጣን፣ ግልጽ እና ተገማች መሆን እንዳለበት አሳስበዋል። ሀገራት በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ውስጥ ያላቸው ውክልና ፍትሃዊ መሆን እንዳለበት ጠቅሰው፤ ውክልናው ተጨባጭ ውጤት ማምጣት እንዳለበትም አስገንዝበዋል።
‎‎በብሪክስ አባል ሀገራት ዘንድ ሀብት፣ ቴክኖሎጂ እና ሰፊ ገበያ አለን-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 12, 2026 137
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ)፦‎‎በብሪክስ አባል ሀገራት ዘንድ ሀብት፣ ቴክኖሎጂ እና ሰፊ ገበያ አለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ጽናትን፣ ፈጠራን፣ ትብብርን እና ዘላቂነትን መገንባት በሚል መሪ ቃል በሕንድ ኒው ዴልሂ እየተካሄደ በሚገኘው 18ኛው የብሪክስ ጉባኤ ላይ አካል በመሆናችን ኩራት ይሰማናል ብለዋል።   ‎‎በብሪክስ አባል ሀገራት ዘንድ ሀብት፣ ቴክኖሎጂ እና ሰፊ ገበያ አለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁን ያለው መልካም ዕድል እነዚህን አቅሞች በማስተሳሰር የላቀ እሴት መፍጠር እና ይህ እሴት ደግሞ ሀብቱ በሚገኝበት ቦታ መመረት እንዲችል ማድረግ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በማዕድን ልማት፣ በታዳሽ ኃይል እና እያደገ በሚገኘው የኢንዱስትሪ መሠረቷ ላይ እነዚህን አጋርነቶች ለመገንባት ዝግጁ ናትም ብለዋል።   ‎‎በተጨማሪም በአሠራር ሥርዓቶቻችን ውስጥ ጽናትን መገንባት፣ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የአህጉራችንን ፍላጎት እንዲያገለግል ማድረግ፣ አስተማማኝ የዕዳ እፎይታ ሒደትን ማሳደግ እንዲሁም የአየር ንብረት ጥበቃ ሥራዎችን ከኢኮኖሚ ሽግግር ጋር ማስተሳሰር ይኖርብናል ሲሉም ገልጸዋል። ‎‎የብሪክስ መድረክ የጋራ ትብብርን ወደ የጋራ እሴት፣ ጽናት እና ዘላቂ ዕድገት የመለወጥ ሰፊ አቅምና ቁርጠኝነት እንዳለውም ነው ያመላከቱት።
በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የተቀረጹት ዘርፎች ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ዕድገት የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው 
Sep 12, 2026 143
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ)፦ በሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የተቀረጹት ዋና ዋና ዘርፎችና ሌሎችም ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ዕድገት የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን የምጣኔ ሀብት ባለሙያው ዘመዴነህ ንጋቱ ገለጹ፡፡ አለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት ባወጣው የቅርብ ጊዜ መረጃ መሰረት፣ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ከተመዘገበባቸው ጥቂት ሀገራት መካከል አንዷ መሆኗን አንስተዋል፡፡ ይህም በሀገሪቱ ከተተገበሩት መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎችና ከተከተለችው የረጅም ጊዜ የልማት ስትራቴጂ የሚመነጭ መሆኑን አመልክተዋል። በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው በተተገበረባቸው ዘርፎች ማለትም በማኑፋክቸሪንግ፣ በግብርና፣ በቱሪዝም፣ በማዕድን እና በቴክኖሎጂ ዘርፎች የተመዘገቡት ውጤቶች አበረታች ናቸው ብለዋል። በተለይም በማዕድን ዘርፍ በሀገሪቱ የታሪክ ሂደት ታይቶ የማይታወቅ ከፍተኛ የወርቅ ኤክስፖርት ገቢ መመዝገቡን የጠቀሱት ባለሙያው፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ ከወርቅ የወጪ ንግድ 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ማግኘት መቻሉ የሪፎርሙ ትልቅ ስኬት መሆኑን አብራርተዋል። በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ የ“ኢትዮጵያ ታመርት” ንቅናቄ ከተጀመረ ወዲህ የሀገር ውስጥ ምርት አቅምን በማሳደግና የማምረት ሂደትን በማጠናከር ረገድ ከነበረበት መነሻ ተነስቶ ከፍተኛ ዕድገት ማሳየቱን ጠቅሰዋል። በግብርናው ዘርፍ ከተለመደው ባህላዊ አሰራር ወደ ዘመናዊና ሜካናይዝድ አሰራር በመሸጋገር ቀደም ሲል በከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ወደ ሀገር ውስጥ ይገቡ የነበሩ ምርቶችን ማስቀረት የተቻለ ሲሆን፣ ምርቶቹን ለውጭ ገበያ ማቅረብ የተጀመረበት አዲስ ምዕራፍ መከፈቱን ተናግረዋል፡፡ በቴክኖሎጂ ዘርፍ ኢትዮጵያ ለቴክኖሎጂው ዘርፍ፣ በተለይም ለአርቲፊሻል ኢንቴሊጀንስ (AI) የሰጠችው ከፍተኛ ትኩረትና የሰለጠነ የሰው ኃይል ማፍራቷ በኦፊሴላዊ መልኩ በአፍሪካ ደረጃ ተወዳዳሪና መሪ የሚያደርጋት ስትራቴጂካዊ እርምጃ ነው ብለዋል። በቱሪዝም ዘርፉ የገበታ ፕሮጀክቶችን ጨምሮ በኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች የተከናወኑት የመሠረተ ልማት ዝርጋታዎችና የመዳረሻ ልማት ሥራዎች የኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ለኢኮኖሚ ዕድገት እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም በአገልግሎት ዘርፍ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም አቀፍ ደረጃ በትርፋማነቱ፣ በኔትወርክ ማስፋፋቱና በስኬታማነት መቀጠሉን ጠቅሰዋል፡፡ በፋይናንስ ዘርፉም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ጨምሮ ሌሎች የግል ባንኮች ያስመዘገቡት በታሪክ ታይቶ የማይታወቅ የትርፍ መጠን በሀገሪቱ የጎላ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ መኖሩን የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል። ሀገሪቱ ለኢኮኖሚ ዕድገት ያላትን መሰረት በማጠናከር ረገድ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ጨምሮ በርካታ የመሰረተ ልማትና የጋዝ ፕሮጀክቶች መጀመራቸውና መጠናቀቃቸው ለኢኮኖሚው ከፍተኛ እንቅስቃሴ መፍጠራቸውን ጠቁመዋል። ለአብነትም የሀገሪቱን የኤሌክትሪክ ኃይል የማመንጨት አቅም ከአምስት ሺህ ሜጋዋት ወደ 10 ሺህ ሜጋዋት ገደማ በእጥፍ ማሳደግ መቻሉን አሳታውቀዋል። የኢትዮጵያ የግል ባለሀብቶች ከሀገር ውስጥ አልፈው በውጭ ሀገራት ኢንቨስት እንዲያደርጉ የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የሀገር ውስጥ የግሉ ዘርፍ አቅሙን አጠናክሮ በመቀጠል በክልሉና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪና ጠንካራ የሚያደርጉ ግዙፍ ኩባንያዎችን መፍጠር እንደሚገባው አሳስበዋል።          
የኢትዮጵያና ብራዚል የኢኮኖሚ፣ ንግድና ኢንቨስትመንት አጋርነት ወደ አዲስና ተስፋ ሰጪ ምዕራፍ እየተሸጋገረ ነው
Sep 12, 2026 163
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያና ብራዚል የኢኮኖሚ፣ ንግድና ኢንቨስትመንት አጋርነት ወደ አዲስና ተስፋ ሰጪ ምዕራፍ እየተሸጋገረ መሆኑን በኢትዮጵያ የብራዚል አምባሳደር ዣንዲር ፈሬራ ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያ የብራዚል አምባሳደር ዣንዲር ፈሬራ ዶስ ሳንቶስ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያና ብራዚል መካከል የኢኮኖሚ፣ የንግድ፣ የኢንቨስትመንት እና የስትራቴጂካዊ ዘርፎች ያለው አጋርነት እየሰፋ መጥቷል። በዚህም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው ግንኙነት ወደ አዲስና ተስፋ ሰጪ ምዕራፍ እየተሸጋገረ ይገኛል ብለዋል። ብራዚል በአፍሪካ የመጀመሪያውን የንግድ እና የኢንቨስትመንት ማስተዋወቂያ ኤጀንሲ (ApexBrasil) ጽሕፈት ቤት በአዲስ አበባ የከፈተች መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የሁለቱን ሀገራት የሁለትዮሽ የኢኮኖሚ፣ የንግድ እና የፖለቲካ ትብብር በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያጠናክረው ገልጸዋል። የብራዚል ባለሀብቶች የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ዕድሎች እና የግል ዘርፍ አቅም እንዲረዱ፣ እንዲሁም ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር የጠበቀ የሁለትዮሽ ትብብር እንዲፈጥሩ ያመቻቻል ብለዋል። የግብርና ዘርፍ የሁለቱም ሀገራት ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት በመሆኑ በቀጣይ ትኩረት ተሰጥቶት ከሚሰሩባቸው ዋነኛ የትብብር መስኮች አንዱ ነው ብለዋል። በተጨማሪም ብራዚል ኢትዮጵያ እየተገበረች ከምትገኘው የ"አረንጓዴ አሻራ" መርሃ-ግብር ትልቅ ተሞክሮ እንደምትወስድ ጠቁመዋል። ባለፉት አራት ዓመታት በአዲስ አበባ በነበራቸው ቆይታ በሀገሪቱ የተመዘገቡ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎችን፣ የሀገራዊ ምክክር ጉባዔን እና የመሠረተ ልማት ዕድገቶችን መታዘባቸውን ገልጸዋል።
‎‎ኢትዮጵያና ማሌዢያ ጠንካራ የኢኮኖሚ አጋርነት ለመመስረት የሚያስችል ከፍተኛ አቅም አላቸው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 12, 2026 124
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2019 (ኢዜአ)፦‎‎ኢትዮጵያና ማሌዢያ ጠንካራ የኢኮኖሚ አጋርነት ለመመስረት የሚያስችል ከፍተኛ አቅም እንዳላቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከብሪክስ ጉባኤ ጎን ለጎን ከማሌዢያ ጠቅላይ ሚኒስትር አንዋር ኢብራሂም ጋር ተገናኝተው ተወያይተዋል። ‎‎ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው፤ በሕዳር 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ካደረጉት ታሪካዊ ጉብኝት የተገኘውን መልካም ዕድል ይበልጥ ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተናል ብለዋል። ‎‎ውይይታቸውም ኢንቨስትመንትን፣ ቱሪዝምን፣ የታዳሽ ኃይል አጋርነትን ማስፋፋት እና ወደ ኮፕ 32 በሚደረገው ጉዞ ላይ ያለውን ትብብር ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ያተኮረ እንደነበር ገልጸዋል። በተጨማሪም በማሌዢያ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት፣ ምርታማነት እና የአምራች ዘርፍ ተሞክሮዎችን መውሰድ በሚቻልባቸው ዕድሎች ዙሪያ መምከራቸውን አስታውቀዋል። ‎‎ኢትዮጵያና ማሌዢያ ጠንካራ የኢኮኖሚ አጋርነት ለመመስረት የሚያስችል ከፍተኛ አቅም አላቸው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህም በኢንቨስትመንት፣ በቴክኖሎጂ፣ በክህሎት እና በዘላቂ ልማት ማዕቀፎች አዳዲስ ዕድሎችን የሚፈጥር ነው ብለዋል።
ታዋቂው ታይም መጽሔት ስለ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ባስነበበው ሰፊ ዘገባው ምን አለ?
Sep 12, 2026 132
በታዋቂው ታይም መጽሔት (TIME Magazine) ላይ እንግሊዛዊው ጸሐፊ ጆሽ ዊልሰን “THE POWER TO UNITE AFRICA” (አፍሪካን የማስተሳሰር ኃይል) በሚል ርዕስ ስለ ግድቡ የተነሱት ዋና ዋና ነጥቦች፡- የአፍሪካውያን ራስን መቻል ማሳያ፡ ግድቡ ከውጭ አበዳሪዎችና ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ድጋፍ ውጪ በኢትዮጵያውያን የገንዘብ አቅምና በቦንድ ግዢ ብቻ መገንባቱ፣ አፍሪካውያን የራሳቸውን ልማት በራሳቸው አቅም ማሳካት እንደሚችሉ ያረጋገጠ ታሪካዊ ፕሮጀክት መሆኑን ቀጣናዊ የኢኮኖሚና የኃይል ትስስር፡ከ5 ሺህ ሜጋ ዋት በላይ የማመንጨት አቅም ያለው ይህ ግድብ፣ የኢትዮጵያን የኤሌክትሪክ ፍላጎት ከማሟላት ባለፈ የኃይል አቅርቦትን ለጎረቤት ሀገራት ተደራሽ በማድረግ የምሥራቅ አፍሪካን የኢነርጂ ገበያ በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያስተሳስር ታላቁ የህዳሴ ግድብ ግዙፍ የልማትና የትብብር ዕድል ከፋችና ቀጣናዊ የጋራ ብልጽግና ማዕከል መሆኑን ለታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ያለው ጠቀሜታ፡የግድቡ የውሃ ፍሰት አስተዳደር የታችኛው ተፋሰስ ሀገራትን የውሃ ፍላጎት የሚያሟላ ለንጹህ አየር እና አካባቢ ጥበቃ፡ፕሮጀክቱ ንጹህ ኢነርጂን ለቀጣናው ሀገራት በማቅረብ የካርቦን ልቀትን ለመቀነስ እና የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎችን ለማጠናከር ቁልፍ ሚና መጫወቱ ለአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ያለው ሚና፡አፍሪካ በመልክዓ ምድራዊ ወሰኖች ሳትታጠር በኢኮኖሚና በመሠረተ ልማት እንድትተሳሰር ለታለመው የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና (AfCFTA) እውን መሆን እንዲህ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ወሳኝ መሆናቸውን የአፍሪካ ትንሳኤ እና አንድነት ዓርማ፡ የፕሮጀክቱ ጅማሮና ሂደት ዜጎች በልማት ላይ ያላቸውን ቀጥተኛ ባለቤትነት በመላው አፍሪካ እንዲስፋፋ ትምህርት የሚሰጥ ስለመሆኑ ግድቡ የአፍሪካ ልማት፣የሕዝቦች ትስስር ቋሚ ድልድይና የራስ መተማመን መንፈስ ዓርማ ሆኖ እንደሚቀጥል በዘገባው ዳስሷል።
የአፍሪካ የልማትና ትብብር ዓርማ - ታላቁ የሕዳሴ ግድብ በታዋቂው ታይም መጽሔት ገጽ
Sep 11, 2026 325
አዲስ አበባ፤ መስከረም 1/2019 (ኢዜአ)፦የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ከኃይል ማመንጫነት በላይ ትርጉም ያለው፣ የአፍሪካን የውስጥ ጥንካሬ መገለጫ እና የቀጣናዊ ትብብር ማሳያ ነው። እንግሊዛዊው ጸሐፊ ጆሽ ዊልሰን በታዋቂው ታይም መጽሔት “THE POWER TO UNITE AFRICA” በሚል ርዕስ ባሰፈረው ጽሑፍ ላይ፣ ይህ ታላቅ ፕሮጀክት በአፍሪካ ታሪክ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑን ገልጿል። አህጉራዊ ትስስርን የማጠናከር አቅም ያለው፣ የቴክኖሎጂን እንዲሁም የኢንዱስትሪ ዕድገትን ጉዞ አሳላጭ የሆነው ይህ ግድብ፣ አስደማሚ በሆነ መልኩ መገንባቱን አመልክቷል። ግድቡ ከተለመዱት ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት እና ከውጭ አበዳሪዎች ውጪ በኢትዮጵያውያን ብቻ መገንባቱ ትልቅ ትምህርት የሚሰጥ አኩሪ ታሪክ ነው።   በቦንድ ግዢና በገንዘብ ድጋፍ የተከናወነው ይህ ፕሮጀክት፣ አፍሪካውያን የራሳቸውን የልማት አጀንዳ በራሳቸው አቅም መደገፍ እንደሚችሉ የሚያሳይ መሆኑ ተጠቅሷል። ከአምስት ሺህ ሜጋ ዋት በላይ የማመንጨት አቅም ያለው የህዳሴው ግድብ ለኢትዮጵያ ኢንዱስትሪያላይዜሽን እና የኤሌክትሪክ ፍላጎት መሟላት ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረክታል። የግድቡ ፋይዳ በኢትዮጵያ ብቻ የተወሰነ ሳይሆን፣ የኃይል አቅርቦትን ለጎረቤት አገራት ተደራሽ በማድረግ የምሥራቅ አፍሪካን የኢነርጂ ገበያ የማስተሳሰር አቅም አለው። ከሀገር ድንበር ባሻገር የሚዘረጉ የኃይል ማስተላለፊያ መስመሮች የቀጣናውን ሕዝቦች የኢኮኖሚ ትብብርና የጋራ ተጠቃሚነት በከፍተኛ ደረጃ ያጠናክራሉ። የህዳሴ ግድብ ንጹህ ኢነርጂ ለቀጣናው አገራት በማቅረብ የካርቦን ልቀት እንዲቀንስ እና የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች እንዲጠናከሩ ቁልፍ ሚና ይጫወታል። ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ይህንን ፕሮጀክት ከጂኦፖለቲካዊ ውዝግብ ማዕቀፍ ወጥቶ እንደ ሰፊ የልማት እና የትብብር ዕድል ሊወስደው እንደሚገባ ጆሽ ዊልሰን ይገልጻል። የኢነርጂ ንግድና የጋራ የውሃ አጠቃቀም ስምምነቶች ሀገራትን ተጠቃሚ የሚያደርግ ኢኮኖሚያዊ ትስስር እንደሚፈጥሩ ሳይንሳዊ ጥናቶችን አብነት በማድረግ ጸሐፊው አስቀምጧል። የውሃ ፍሰት አስተዳደርን ከኤሌክትሪክ ንግድ ጋር መተሳሰሩ በታችኛው ተፋሰስ የሚገኙ አገሮችን የውሃ አቅርቦት ፍላጎት ከማሟላት ባለፈ የጋራ ዕድገትን እውን እንደሚያደርግ አመልክቷል።   ግድቡ በረጅም ጊዜ የድርቅ ወቅት ሊፈጠሩ የሚችሉ አስቸጋሪ ሁኔታዎችን በጋራ ለመመከት የሚያስችል ቋሚ የቴክኒክ ትብብርና የመረጃ ልውውጥ መንገድ ይከፍታልም ነው ያለው። አፍሪካ ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ለማስመዝገብ ትላልቅ የመሠረተ ልማት ፕሮጀክቶች ያስፈልጓታል፤ የህዳሴ ግድብም ለዚህ ትልቅ ማሳያ የሆነ ግዙፍ ፕሮጀክት ነው ሲልም ገልጿል። አፍሪካ በመልክዓ ምድራዊ ወሰኖች ሳትታጠር በኢኮኖሚና በመሠረተ ልማት የማስተሳሰር ትልም ያለው የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና እውን እንዲሆን እንደ ህዳሴ ግድብ ያሉ ፕሮጀክቶች ወሳኝ ድርሻ አላቸው። ግድቡ አፍሪካውያን የራሳቸውን ጉዳዮች በዲፕሎማሲያዊ ብስለትና በሰላማዊ መንገድ የመፍታት አቅም እንዳላቸው የሚያሳይ ነውም ብሏል። ጆሽ ዊልሰን በጽሑፉ ላይ እንዳሰፈረው፣ የውሃ ሀብት የግጭት መፍጠሪያ ሳይሆን የጋራ ብልጽግና ማዕከል መሆን አለበት። የአፍሪካ ኅብረት መርሆዎችን መሰረት በማድረግ፣ የጋራ ሀብቶች ለጋራ ብልጽግና እንዲውሉ ማድረግ የዘመኑ የዲፕሎማሲ እና የልማት ዋና ትኩረት ሊሆን ይገባል ነው ያለው።   ጆሽ ዊልሰን በጽሑፉ ላይ እንዳሰፈረው፣ የውሃ ሀብት የግጭት መፍጠሪያ ሳይሆን የጋራ ብልጽግና ማዕከል መሆን አለበት። የአፍሪካ ኅብረት መርሆዎችን መሰረት በማድረግ፣ የጋራ ሀብቶች ለጋራ ብልጽግና እንዲውሉ ማድረግ የዘመኑ የዲፕሎማሲ እና የልማት ዋና ትኩረት ሊሆን ይገባል ነው ያለው። የህዳሴ ግድብ ስያሜ በራሱ የአፍሪካን ትንሳኤ እና የራስ መተማመን መንፈስ የሚያንጸባርቅ መሆኑን አመልክቷል። ግድቡ ዜጎች በልማት ላይ ያላቸው ቀጥተኛ የባለቤትነት ስሜት በመላው አፍሪካ እንዲስፋፋ እና የሀገር ውስጥ የፋይናንስ ገበያዎች እንዲጠናከሩ በር ይከፍታል። ጆሽ ዊልሰን ጽሑፉን ሲያጠቃልል፣ የህዳሴው ግድብ የአፍሪካ ልማትና አንድነት እንዲሁም ሕዝቦችን የሚያስተሳስር ቋሚ ድልድይና ዓርማ ሆኖ ይቀጥላል ሲል ገልጿል።
የሀዋሳ ከተማ የተቸረችውን የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ አልምቶ ለመጠቀም በተከናወኑ ተግባራት ውጤት ተመዝግቧል
Sep 10, 2026 282
ሀዋሳ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የሀዋሳ ከተማ የተቸረችውን የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ አልምቶ ለመጠቀምና ለህዝብ ጥቅም ለማዋል በተከናወኑ ተግባራት ውጤት መመዝገቡን ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለጹ፡፡ የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ግንባታ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የምስጋናና የዕውቅና መርሀ ግብር እየተካሔደ ነው።   ''ሀዋሳ ታመሰግናችኋለች'' በሚል መሪ ቃል የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞና ሌሎች ከፍተኛ የሥራ ሀላፊዎች በተገኙበት ነው መርሃ ግብሩ እየተካሔደ የሚገኘው። የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ እንደገለጹት በ2018 በጀት ዓመት የታቀዱ ተግባራት በቅንጅት ተከናውነው ውጤት ያስገኙበት ነው። ከተማዋ የተቸረችውን የተፈጥሮ ሀብት በአግባቡ አልምቶ ለመጠቀምና ለህዝብ ጥቅም ለማዋል የተደረገው ጥረት ተስፋ ሰጪ ውጤት ማስመዝገቡን አንስተዋል። ከእነዚህም አንዱ የሐይቅ ዳር ልማት ፕሮጀክት መሆኑን አንስተው በመንግስትና በአጋር አካላት ተሳትፎ ግንባታው እየተፋጠነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።   ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ የከተማዋን ገጽታና ውበት እንዲሁም ተወዳዳሪነትና ተመራጭነትን በማሳደግ ረገድ ትርጉም ያለው ውጤት እንደሚኖረው ተናግረዋል። በዚህ የልማት ሥራ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ የሚገኙ አካላትን ያመሰገኑት ከንቲባው የዛሬው የምስጋናና ዕውቅና መርሀ ግብር የተዘጋጀው ተሳትፎውን የበለጠ ለማጠናከር መሆኑን አስረድተዋል። በመርሀ ግብሩ ላይ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ ካቢኔ አባላት፣ባለሀብቶች፣የሀገር ሽማግሌዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
በግንባታ ላይ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ለነገዋ ኢትዮጵያ ጠንካራ መሰረት የሚያኖሩ ናቸው- ወጣቶች
Sep 10, 2026 158
‎ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ በግንባታ ላይ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ለነገዋ ኢትዮጵያ ጠንካራ መሰረት የሚያኖሩ መሆኑን በሀዋሳ ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው ወጣቶች ገለጹ። ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቁን ተከትሎ ሌሎች የሀገርን እድገትና ብልጽግና ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች በመከናወን ላይ ይገኛሉ። በግንባታ ላይ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያን በላቀ መልኩ ወደ ፊት የሚያራምዱ እና ለቀጣዩ ትውልድ ብሩህ ተስፋ የሰነቁ መሆናቸው ይታመናል። የነገዋን ኢትዮጵያ የሚወስኑት እነዚህ የልማት ፕሮጀክቶች ከሀገራዊ ፋይዳም የተሻገረ ቀጣናዊና አህጉራዊ ጠቀሜታ የሚኖራቸው ናቸው። ከግዙፍ ፕሮጀክቶቹ መካከል የቢሾፍቱ አውሮፕላን ማረፊያ፣ የኒውኩለር ማብላያ፣ የጋዝ ፋብሪካ፣ ማዳበሪያ ፋብሪካ፣ የ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ይጠቀሳሉ። እነዚህ ግዙፍ ፕሮጀክቶችና ሌሎችም እየተከናወኑ ያሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች የነገዋ ኢትዮጵያ ፅኑ መሰረትና የትውልዱ ብሩህ ተስፋ የሚሆኑ ናቸው። በሌላ በኩል ወጣቱን ትውልድ በቴክኖሎጂ ተጠቃሚ በማድረግ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆን ለማስቻል እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች የነገዋን ኢትዮጵያ ለመገንባት መሰረት የሚጥሉ ናቸው። በፖለቲካና ዲፕሎማሲ መስኮች የሚከናወኑ ሀገራዊ ጉዳዮችም የነገዋን የበለጸገች ኢትዮጰያ ለመገንባት ተስፋ የተሰነቀባቸው መሆኑን መግለፅ ይቻላል። ከዚሁ ጋር በተገናኘ ኢዜአ ያነጋገራቸው የሀዋሳ ከተማ ወጣቶች በመደመር መንግስት እየተከናወኑ ያሉ ሀገራዊ ኢንሼቲቮችና ግዙፍ ፕሮጀክቶች የነገዋ ኢትዮጵያ ጠንካራ መሰረቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወጣት በቃሉ መሠረት፤ ታላቁ የህዳሴ ግድብ፣ የጉባ ብስራቶች፣ የገበታ ፕሮጀክቶች፣ የኮሪደር ልማት ሥራዎችና ሌሎች ሀገራዊ ፕሮጀክቶች ዛሬን ብቻ ሳይሆን ነገንም ጭምር ታሳቢ ያደረጉ መሆናቸውን አንስቷል። የኢትዮጵያ የወደፊት እጣ ፈንታ ላይ ለመወሰን በተለይም የወጣቶች ጠንካራ ተሳትፎ አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሶ በዲጂታል ዘርፍ ግንባር ቀደም ተሳታፊ የሚሆንበት መደላድል መፈጠሩ ጥሩ ጅምር መሆኑን ተናግሯል።   ሌላኛው ወጣት ኃይለኢየሱስ ታምራት፤ በመደመር መንግስት እየተከናወኑ ካሉ ነገን ታሳቢ ያደረጉ ተግባራት መካከል የጠንካራ ተቋማት ግንባታ ሥራዎች ኢትዮጵያን ሊያሻግሩ የሚችሉ ናቸው ብሏል፡፡ ለአብነት በስኬት መከናወን የቻለው ሀገራዊ ምክክር በመነጋገር ላይ የተመሰረተ አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍን የከፈተ ፣ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በዕኩልነት ለነገይቱ ኢትዮጵያ ሀሳብ ያዋጣበት መሆኑን ገልጿል፡፡ ወጣት ትዕግስት ፍስሀ በበኩሏ የመደመር መንግስት የኢትዮጵያ የህልውናና የነገ እጣ ፈንታ የሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮችንም በመተግበር በኢኮኖሚ የተሻለ ተወዳዳሪ የሆነች ሀገር ለመገንባት እየሰራ መሆኑን ተናግራለች፡፡ የባህር በር ባለቤትነትን ለማረጋገጥ አሁን ላይ እየተከናወኑ ያሉ ዓለም ዓቀፍ መርህን መሰረት ያደረጉ እንቅስቃሴዎች ኢትዮጵያን ከፍ የሚያደርጉ ተግባራት መሆናቸውን ጠቅሳለች፡፡ የባህር በር ባለቤትነት ለነገይቱ ኢትዮጵያ ዘርፈ ብዙ አንድምታ ያለው መሆኑን የተናገረችው ወጣት ትዕግስት፣ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠርና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞች በማስገኘት ረገድ ትልቅ ተስፋ የሚጣልበት ተግባር መሆኑን አመላክታለች፡፡ መንግስት በሁሉም ዘርፎች እያከናወናቸው ያሉ ስኬታማ ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የበኩላቸውን እንደሚወጡ ወጣቶቹ አረጋግጠዋል፡፡      
በኢትዮጵያ እየተመዘገበ ያለው ፈጣን እድገት በትውልዱ ዘንድ ብሩህ ተስፋ እና የላቀ ተነሳሽነት ፈጥሯል
Sep 10, 2026 149
ጂንካ፤ ጷግሜን 5/2018 (ኢዜአ፡-በኢትዮጵያ በየዘርፉ እየተመዘገበ ያለው ፈጣን እድገትና ለውጥ በትውልዱ ዘንድ ብሩህ ተስፋ እና የላቀ ተነሳሽነትን መፍጠሩን የጂንካ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተገነቡና በግንባታ ላይ ያሉ ሜጋ ፕሮጀክቶቹ የአሁኑን ትውልድ ብቻ ሳይሆን የመጪውን ብሩህ ጊዜ ታሳቢ ያደረጉ ስለመሆናቸውም ነዋሪዎቹ ተናግረዋል። "የነገ ቀን" ጳጉሜን-5 በሀገሪቱ በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ይገኛል፡፡ ቀኑን አስመልክቶ ኢዜአ በጂንካ ከተማ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች እንዳሉት ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ውስጥ እያስመዘገበች ያለው ፈጣን እድገትና ለውጥ ትውልዱ በነገዋ ኢትዮጵያ ቀን ብሩህ ተስፋ እንዲሰንቅ የላቀ ተነሳሽነት ፈጥሯል፡፡ ከነዋሪዎቹ መካከል የጂንካ ሁለተኛና መሰናዶ ትምህርት ቤት መምህር ሀብታሙ አያሌው እንዳሉት ሀገራችን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በግብርናው፣ በኢንዱስትሪ፣ በቴክኖሎጂና በቱሪዝም ዘርፎች ተጨባጭ የሆነ ፈጣን እድገት አስመዝግባለች። በሀገሪቱ የተገነቡና እየተገነቡ ያሉ ሜጋ ፕሮጀክቶች ለነገዋ ኢትዮጵያና ለዜጎቿ ብሩህ ተስፋ መሆናቸውን ገልጸው፣ የሕዳሴው ግድብ፣ የቢሸፍቱ ዓለም አቀፍ ኤርፖርት፣ የአረንጓዴ ልማት ሥራዎችና ሌሎች ግዙፍ ፕሮጀክቶች ሀገራዊ እድገትን በማፋጠን በየዘመኑ ትውልድን ተጠቃሚ ያደርጋሉ ብለዋል። በተለይ በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር፣ በቱሪዝም ዘርፍ፣ በዲጂታል ኢትዮጵያ እና በገበታ ለሀገርና ለትውልድ የተከናወኑ ስኬታማ የልማት ተግባራት ተጨባጭ ለውጥ ያመጡና በትውልዱ ዘንድ ተነሳሽነትን የፈጠሩ ናቸው ብለዋል።   ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ታምራት ምናስ፣ በኢትዮጵያ በመከናወን ላይ ያሉ ሜጋ ፕሮጀክቶች እና ዲጂታል ቴክኖሎጂ ለዜጎች ብዙ ተስፋና ዕድሎች ይዘው መጥተዋል ብለዋል። በሴራ ያጣነውን የባህር በር ባለቤትነት የማስመለስ ጥረትን ጨምሮ ኢትዮጵያ ያላትን ሀብት በማልማት ከድህነት እንድትወጣ በተከናወኑ ሥራዎች እየተመዘገበ ያለው ውጤት በትውልዱ ዘንድ ተስፋን የሚያጭር ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በየዘርፉ እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶች መጪው ዘመን ለኢትዮጵያ ብሩህ እንደሆና ያሳያሉ ያሉት አቶ ታምራት፣ የኢትዮጵያን አድገት በላቀ ተነሳሽነት እና ትጋት ለማስቀጠል የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁነታቸውን አረጋግጠዋል።   ወጣት በቃህኝ ጥላሁን በበኩሉ በኢትዮጵያ እየተከናወኑ ያሉ ትላልቅ ግዙፍ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች በወጣቱ ዘንድ ተስፋን ያጫሩ እና ለነገ ተነሳሽነቱን የያሳደጉ ናቸው ብሏል። ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተከናወኑ ሥራዎችና በመከናወን ላይ ያሉ ተግባራት ከሀጋራዊ ፋይዳቸው ባለፈ በተለይ ወጣቱን ከቴክኖሎጂ ጋር በማስተዋወቅ ተጠቃሚ እያደረጉ መሆናቸውን ተናግሯል። ወጣቱ በዲጂታል ኢትዮጵያ የቴክኖሎጂ አቅሙን ከማሳደግ ባለፈ ለሥራ ዕድል ፈጠራ በማዋል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን እያሳደገ ጭምር መምጣቱንም ገልጿል። ኢትዮጵያ የተሻለች፣ የበለጸገች እና በቴክኖሎጂ ራሷን የቻለች ሀገር ለማድረግ ዛሬ እየተሰሩ ያሉ ሥራዎች የሀገሪቱን የነገ ብሩህ ተስፋ እያለመለሙ በመሆኑ መጠናከር እንዳለባቸው ተናግሯል።  
የሞጆ ሎጂስቲክስ ማዕከል የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ማብሰሪያ፣ የቀጣናው ማስተሳሰሪያ እና የመደመር እሳቤ ፍሬ ማሳያ ነው
Sep 10, 2026 183
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የሞጆ ሎጂስቲክስ ማዕከል የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ማብሰሪያ፣ የቀጣናው ማስተሳሰሪያ እና የመደመር እሳቤ ፍሬ ማሳያ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ መርቀው በይፋ ሥራ አስጀምረዋል። በመርሀ ግብሩ ላይ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ፣ የኢፌዴሪ ጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል የሀገራችን የደም ስር ነው። የትራንስፖርትና የሎጂስቲክስ አገልግሎት ችግሮችን መፍታት የሚያስችል የማዕዘን ድንጋይ መሆኑን ገልጸዋል። ማዕከሉ የሁለንተናዊ ልማትና ብልፅግና ማረጋገጫ የመደመር መንግሥት ስኬት አይነተኛ ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘርፉን ማነቆ በተመለከተ የሰጡት አቅጣጫ ፍሬ ማፍራቱ ማሳያ ነው ብለዋል። የሞጆ ሎጂስቲክስ ማዕከል የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ማብሰሪያ፣ የቀጣናው ማስተሳሰሪያ እና የመደመር እሳቤ ፍሬ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ የሎጂስቲክ ማዕከል እናደርጋታለን ያሉት ቃል በተግባር እውን እንዲሆን ያስችላል ያሉት ሚኒስትሩ፤ በማዕከሉ ሁለት የባቡር መስመሮች መዘርጋታቸውን ተናግረዋል። የወጭና ገቢ ንግድ ዕቃዎችን የሚያስተናግዱ መጋዘኖች የያዘና በአንድ ጊዜ በርካታ የጭነት አገልግሎት መስጠት ያስችላል ብለዋል። አርሶ አደሮች ምርታቸው ሳይበላሽ ለውጭ ገበያ ማቅረብ የሚችሉበትን ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል።
የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል በመደመር እይታ የሚመራው መንግሥት በሁሉም ዘርፎች ምርትና ምርታማነትን እያሳደገ ለመሆኑ ትልቅ ማሳያ ነው
Sep 10, 2026 150
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ ፕሮጀክት በመደመር እይታ የሚመራው መንግሥት በሁሉም ዘርፎች ምርትና ምርታማነትን እያሳደገ ለመሆኑ ትልቅ ማሳያ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ ፕሮጀክትን መርቀው በይፋ ሥራ አስጀምረዋል።   በዚሁ የምርቃት መርሃ ግብር ላይ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ፣ የኢፌዴሪ ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ እንግዶች ተገኝተዋል። የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የመደመር መንግሥት ባለፉት ዓመታት በሁሉም ዘርፎች ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ ጥራት ያለው ምርት ለማምረት እንዲሁም ምርቶችን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ በብቃት ለማቅረብ የመደመር እይታን መሠረት አድርጎ ሲሠራ ቆይቷል። በግብርናና በኢንዱስትሪ ዘርፎች የሚመረቱ ምርቶች የሚፈለገውን የጥራት ደረጃ ጠብቀው ለገበያ እንዲቀርቡ በቂ የሎጂስቲክስ አቅርቦት አለመኖሩን አስታውሰዋል፡፡   ይህንን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ባለፉት ዓመታት በርካታ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቁመው፤ በተለይም ዘመናዊና በቂ የማከማቻ መጋዘኖች እንዲገነቡ፣ የመንገድ መሠረተ ልማቶች እንዲዘረጉ እና ለሎጂስቲክስ ዘርፉ አስፈላጊ የሆኑ ተሽከርካሪዎች እንዲቀርቡ መደረጉን ገልጸዋል። ከዚህም በተጨማሪ እንደ አቮካዶና ሙዝ ያሉ በቀላሉ የሚበላሹ የግብርና ምርቶችን ጥራታቸውን ጠብቆ ወደ ውጭ ገበያ ለመላክ የሚያስችሉ የቀዝቃዛ ኮንቴይነሮችን ለማቅረብ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ዛሬ በሞጆ ተመርቆ ሥራ የጀመረው ፕሮጀክት በምርታማነት ዘርፍ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍትና የኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ከፍ የሚያደርግ ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የሀገርን ቀጣይ ተስፋ እና የትውልዱን እጣ ፋንታ የተሻለ ለማድረግ የዛሬው ብርታትና ትጋታችን ወሳኝ ነው- ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Sep 10, 2026 103
ባሕርዳር፤ ጳግሜ 5/ 2018 (ኢዜአ) ፡-የሀገርን ቀጣይ ተስፋ እና የትውልዱን እጣ ፋንታ የተሻለ ለማድረግ የዛሬው ብርታትና ትጋታችን ወሳኝ ነው ሲሉ የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። ጳጉሜን 5 የነገው ቀን በአማራ ክልል በተለያዩ መርሃ ግብሮች እየተከበረ ይገኛል።   በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርእሰ መሥተዳድር አረጋ ከበደ፤ የነገውን የሀገርን ተስፋ እና የትውልዱን እጣ ፋንታ የተሻለ ለማድረግ የዛሬው ብርታትና ትጋታችን ወሳኝ ነው ብለዋል። የዛሬው ትጋታችን ለነገ ከተስፋም ባለፈ ፍሬ የሚያፈራ በመሆኑ በሁሉም ረገድ የጀመርናቸው የልማት ስራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አፅኖት ሰጥተዋል። የክልሉ መንግሥት የነገውን ትውልድና የሀገር ተስፋ በማሰብ የአሻጋሪ ዕድገት እና የዘላቂ ልማት አቅዶችን ለማሳከት የተቀናጀ ጥረት እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል።   የነገ ዋስትናችን ዛሬ በመሆኑ የቀጣዩን ትውልድ ተስፋ ለማሳመር በቴክኖሎጂና ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ላይ በማተኮር መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። ርእሰ መስተዳድሩ በማጠቃለያ መልእክታቸው አዲሱ ዓመት ለክልሉ ህዝብና ለመላው ኢትዮጵያዊያን የሰላም፣ የፍቅርና የስኬት እንዲሆን ተመኝተዋል።  
በክልሉ የሚገኙ እምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት የዜጎችን ተጠቃሚነት እውን የማድረግ ጥረት ይቀጥላል
Sep 10, 2026 181
አሶሳ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሚገኙ እምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት ሁለንተናዊ እድገትና የዜጎችን ተጠቃሚነት እውን የማድረግ ጥረት ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን በብልጽግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽህፈት ኃላፊ ኢሳቅ አብዱልቃድር ተናገሩ። የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ጳጉሜን 5 (የነገ ቀን) ምክንያት በማድረግ በአሶሳ ከተማ የግራናይት ፋብሪካ እና የቀርከሃ ፋብሪካዎች የስራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል።   በጉብኝቱ ላይ የተገኙት በብልጽግና ፓርቲ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኢሳቅ አብዱልቃድር፤ በክልሉ የተጀመሩ ሁለንተናዊ የልማት ስራዎች ትልቅ ተስፋ የተሰነቀባቸው መሆኑን ገልጸዋል። በጉብኝቱ ያረጋግጥነው ይህንኑ ነው ያሉት ሃላፊው በክልሉ የሚገኙ እምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት ሁለንተናዊ እድገትና የዜጎችን ተጠቃሚነት እውን የማድረግ ጥረት ይቀጥላል ብለዋል። በክልሉ በተለይም ወጣቶች የስራ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑና በዲጂታል ቴክኖሎጂ የዳበረ እውቀት እንዲኖራቸው ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። ባለፋት ዓመታት የተከናወኑ የልማት ስራዎች የነገዋን ኢትዮጵያ የብልጽግና ጉዞ የሚያረጋግጡ መሆናቸውን እና የዜጎችን ተጠቃሚነት በተግባር ያሳዩ መሆናቸውንም ገልጸዋል። በክልሉ የግብርናውን፣ ማዕድንና የማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት እየተመዘገበ እንደሆነም ተናግረዋል።   በመርሃ ግብሩ በክልሉ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ጉዞ እና የኢንቨስትመንት አማራጮችን ማልማት ላይ ያተኮረ የፓናል ውይይት ተካሂዷል።
ኢትዮጵያን የአፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራትን አጠናክረን እንቀጥላለን-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 10, 2026 137
ኢዲስ አበባ ፤ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያን የአፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራትን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያን ዕድገትና ልማት ሊያስቆሙ የሚሞክሩ ኃይሎችን ከማይችሉት ተራራ ጋር እየታገሉ መሆኑን በተግባር እናሳያቸዋልን ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያን መርቀው በይፋ ስራ አስጀምረዋል። በመርሀ ግብሩ ቀዳማዊት እመቤት ዝናሽ ታያቸው፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ፣ የኢፌዴሪ የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።   በምረቃ መርሃ ግብሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ባስተላለፉት መልዕክት ኢትዮጵያን የአፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራትን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። ባለፉት ጥቂት ወራት የተመዘገቡ በርካታ ስኬቶች ለነገዋ ኢትዮጵያ መሰረት የሚጥሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል። በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ከ50 ሚሊዮን የሚልቁ ዜጎች ድምፅ በመስጠት ለቀጣዮቹ አምስት ዓመታት የሚመራቸውን መንግሥት የመረጡበት፣ ከኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦች የተውጣጡ አራት ሺህ ዜጎች በጋራ መክረውና ዘክረው የኢትዮጵያን መፃኢ ጊዜ የወሰኑበት፣ ስምንት ነጥብ ሁለት ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል ጠቅላላ ድምሩን 56 ቢሊዮን ማድረስ የተቻለበት ዓመት መሆኑንም ተናግረዋል። እነዚህ የስምረት የድልና የመከናወን ስኬቶች ተሰናስለው ኢትዮጵያ ከ10 ነጥብ 2 በመቶ በላይ ዕድገት እንድታስመዘግብ አስችሏታል ብለዋል። እንደ ኢትዮጵያ ሰፊ ህዝብ ያለው ሀገር ለማደግ ሎጂስቲክስ ከፍተኛ ጉልበት እንዳለውም ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የገለጹት።   ሎጂስቲክስ ከትራንስፖርት፣ ወደብ፣ የባቡር መሰረተ ልማት ለአርሶ አደሩ እስከሚደርስ ያለውን ሰንሰለት የያዘ መሆኑን ገልጸው፤ ለኢትዮጵያ ዕድገት ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። የሎጂስቲክስ አገልግሎት ችግር የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ አንቆ የቆየ መሆኑን በማንሳት፣ የሞጆ ሎጂስቲክስ ማዕከል እነዚህን ችግሮች እንደሚፈታ ገልጸዋል። የሞጆ የሎጂስቲክስ ማዕከል የኮንቴነር የመያዝ አቅም ከ500 ሺህ ወደ አንድ ሚሊዮን ያሳድጋል ብለዋል። የኢትዮጵያ ዕድገት የተሟላ እንዲሆን ሁሉም ማዕዘናትን ከጫፍ ጫፍ ማገናኘት እንደሚገባ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያስገነዘቡት። በ2018 ዓ.ም የብዙ ድል፣ ስኬትና መከናወን ዘመን እንደነበር ገልጸው፤ በ2019 ዓ.ም የላቀ የምንፈፅምበት ዓመት እንደሚሆን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሰላም እንደሚሻሻል ጠቁመው፤ ከጀመርነው ዕድገትና ልማት ሊያስቆሙን የሚሞክሩ ኃይሎችን ከማይችሉት ተራራ ጋር እየታገሉ መሆኑን በተግባር እናሳያቸዋለን ሲሉም ገልጸዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፤ኢትዮጵያን የአፍሪካ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። ልጆቻችን የተሻለች ሀገር እንዲረከቡ ያለብንን አደራ በሙሉ ዕምነትና ብቃት እናከናውናለን ሲሉም ተናግረዋል።
አዲሱ ዓመት ሀገራዊ አንድነታችንን በማጠናከር በላቀ የስራ መንፈስ የተጀመሩ ሁሉን አቀፍ የልማት ስራዎች የሚጎለብቱበት ነው
Sep 10, 2026 78
ሐረር ፤ዻጉሜ 5/2018 (ኢዜአ) ፡-አዲሱ ዓመት ሀገራዊ አንድነታችንን በማጠናከር በላቀ የስራ መንፈስ የተጀመሩ ሁሉን አቀፍ የልማት ስራዎች የሚጎለብቱበት ነው ሲሉ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ተናገሩ፡፡ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ በክልሉ “የነገ ቀን” በተከበረበት ዕለት አዲሱን ዓመት ምክንያት በማድረግ ባስተላለፉት መልዕክት የ2018 ልዩና ታሪካዊ ዓመት ነው ሲሉ ተናግረዋል።   ለዚህም 7ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ፣ ዲሞክራሲያዊና ነፃ በሆነ መልኩ አካሂደን ህዝቡ የሥልጣን ባለቤትነቱን በድምፁ ያረጋገጠበት ታላቅ የዲሞክራሲ መድረክ ያካሄድንበት ነው ብለዋል። ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር በፍቅርና በጋራ የተሠራበት ማህበራዊ መሰረት በመጣሉ ሀገራዊ መግባባታችን መጎልበቱን ተናግረዋል፤ ለዘመናት የቆዩ መሠረታዊ ልዩነቶቻችንን በውይይትና በሰለጠነ መንገድ ለመፍታት፣ ብሔራዊ መግባባትን ለመገንባትና ለዘላቂ ሰላም መሠረት ለመጣል የተቻለበት ነው ብለዋል። ከፖለቲካና ዲሞክራሲያዊው ሂደት ጎን ለጎን፣ የዜጎቻችንን ህይወት የሚያሻሽሉ ታላላቅ የማህበራዊና የኢኮኖሚ ልማት ስራዎች በስፋት የተከናወኑበት ዓመትም ነው ሲሉ ገልጸዋል። ገፅታ የሚቀይሩ የኮሪደር ልማቶች፣ የቱሪዝም መስህቦችና ሰው-ተኮር ፕሮጀክቶች በፍጥነት ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁበት እንደነበረም አንስተዋል። የግብርናና የአካባቢ ልማት ስራ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ሀገራዊ የምግብ ዋስትናችንን እያረጋገጥን እንገኛለን ሲሉም ነው የተናገሩት። ዓመቱ ከፍተኛ መነሳሳትና ቁርጠኝነት የታየበት፣ የመላው ህዝባችን ንቁ ተሳትፎና ተጠቃሚነት የተረጋገጠበት መሆኑንም አንስተዋል። ቀጣዩ 2019 ዓ.ም ሀገራዊ አንድነታችንን የምናጠናክርበት፣ የሕግ የበላይነትን የምናረጋግጥበትና ጠንካራ የልማት መሠረት የምንጥልበት ዓመት ነው ብለዋል። የከተማና የገጠሩ ነዋሪ ህዝቦች ሁለንተናዊ እና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ልዩ ትኩረት ይሰጣቸዋል ሲሉ አስገንዝበዋል። በዚህም የከተማ እና የገጠር የኮሪደር እና የመሰረተ ልማት ስራዎች፣ የቅርስ እና የቱሪዝም መስህቦች ጥበቃ፣ የውበት እና ጽዳት ስራዎች፣ የመልሶ ማልማት፣ የግብርና ማዘመንና ምርታማነትን ማሳደግን ጨምሮ የቴክኖሎጂ ተጠቃሚነትን የማሳደግ ተግባራት ተጠናክረው የሚቀጥሉ ይሆናል ነው ያሉተ። የክልሉን ሰላምና የህግ የበላይነት ይበልጥ በማጠናከር የህዝቡን የመቻቻልና የአብሮነት እሴት የማጠናከር ስራም ትኩረት የሚሰጠው እንደሚሆን ነው ያብራሩት። በክልሉ ህዝቦች መካከል ለዘመናት ስር የሰደዱት የአብሮነት፣ የመከባበር፣ የወንድማማችነትና የእህትማማችነት አኩሪ እሴቶች በፀና አለት ላይ መትከልም የመደበኛ እቅዶች አካል እንደሚሆን ነው ያመለከቱት። የኑሮ ውድነት ጫናን የማቃለል፣ የስራ እድል ተጠቃሚነትን የማጎልበት፣ የግል ዘርፉ በኢንዱስትሪና አገልግሎትመስኮች ያለው ተሳትፎ እንዲጠናከር ይደረጋል ብለዋል። ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ከመሰረታቸው ለመንቀል ግልፅና ተጠያቂነት ያለው የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት መዘርጋትና የስራ ውጤታማነትን ማረጋገጥ ሌላው የአዲሱ ዓመት ቁልፍ ተግባራችን ነው ሲሉም ገልጸዋል። በመጨረሻም አዲሱ ዓመት የፍቅር፣ የመቀራረብ፣ የመተማመን፣ የአንድነት፣ የትጋት እና የብልፅግና ዓመት እንዲሆን ተመኝተዋል።  
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ60 ሄክታር መሬት ላይ የተገነባውን ዘመናዊ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ የመጀመሪያ ምዕራፍ መረቀው ከፈቱ
Sep 10, 2026 101
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ60 ሄክታር መሬት ላይ የተገነባውን ዘመናዊ የሎጂስቲክስ ማዕከል ማስፋፊያ የመጀመሪያ ምዕራፍ መረቀው ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ በሞጆ ተገኝተው በምረቃው ላይ ባስተላለፉት መልዕክት ግንባታውን ኢትዮጵያ የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና ጉዞ፡ በተግባር የታነጸበት ስራ ሲሉ ገልጸውታል።   ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት በዓመት እስከ 1 ሚሊዮን ባለ 20 ጫማ ኮንቴነሮችን የማስተናገድ አቅም ያላቸው ጣቢያዎችና ዘመናዊ መጋዘኖች ያሉት መሆኑንም ገልጸዋል። የደረቅ ብትን ጭነቶችን በሀገር ውስጥ እንድናሽግ ማስቻሉ፣ የውጭ ምንዛሬን ከመቆጠብ ባለፈ ለዜጎቻችን ሰፊ የሥራ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። የማዕከሉን የአሰራር ፍጥነት ለማሳደግ በሀገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ የተተከለው የባቡር ላይ ክሬን ከባቡር መስመር የሚደረገውን የኮንቴነር ዝውውር በከፍተኛ ፍጥነት ያከናውናል ሲሉም ገልጸዋል።   ሙሉ አሰራሩ በዘመናዊ ዲጂታል መሰረተ ልማት የተሳሰረ በመሆኑ፣ ለተገልጋዮች ፈጣን እና አስተማማኝ አገልግሎትን ያሳልጣል። ይህ ማዕከል ከኢትዮ-ጅቡቲ መስመር ባሻገር ኢትዮጵያን፣ ደቡብ ሱዳንን እና ዩጋንዳን የሚያስተሳስረው የ‘ደሱ’ ኮሪደር አካል ሲሆን፤ ይህም ሀገራችን በዓለም አቀፍ የሎጂስቲክስ ደረጃ ላይ ያላትን ስፍራ የሚያሻሽልና የቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስራችንን ወደ አዲስ የዕድገት ምዕራፍ የሚያሸጋግር ትልቅ ድል ነው ብለዋል።  
የኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር መመለስ ለዓለም አቀፍ የባሕር ላይ ንግድ መስመር ደህንነት አስፈላጊ ነው - በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሤ (ዶ/ር)
Sep 10, 2026 143
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር መመለስ ለዓለም አቀፍ የባሕር ላይ ንግድ መስመር ደህንነት እና ለቀጣናው ኢኮኖሚ ዕድገት አስፈላጊ መሆኑን በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አብርሃም ንጉሤ (ዶ/ር) ገለጹ። እስራኤል የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥያቄ የምትደግፈው መሆኑንም አስታውቀዋል። አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ እና እስራኤል ታሪካዊ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ወደ ላቀ አጋርነት እየተሸጋገረ ነው። በዚህም የመንግሥት ለመንግሥት፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች እንዲሁም በንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ከፍተኛ ዕድገት እየተመዘገበ መሆኑንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በማደግ ላይ የምትገኝ ሀገር ናት ያሉት አምባሳደሩ፤ ለዚህም የኢትዮጵያን ወጪና ገቢ ንግድ የሚያሳልጥ የባሕር በር ከሌለ ዕድገትን ለማፋጠን አዳጋች ነው ብለዋል። ለዚህም ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነትን ለማረጋገጥ ላቀረበችው ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥረት እስራኤል በሙሉ ድጋፍ እንደምታደርግ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር መመለስ የባሕር ላይ ሽብርተኞችንና ወንበዴዎችን በመመከት ለዓለም ሰላም እና የኢኮኖሚ ዕድገት ጥሩ ውጤት የሚያመጣ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት የሁለቱን ሀገራት ጂኦ ስትራቴጂክ ተጠቃሚነትን በማጎልበት ቀጣናዊ የሽብር ስጋቶችን በአስተማማኝ ሁኔታ ለመቀልበስ ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረውም አምባሳደሩ አስረድተዋል። ሽብርተኞች በቀይ ባሕር ስትራቴጂክ የንግድ መስመር በመርከቦች ላይ በሚፈጽሙት ጥቃት ምክንያት በንግድ ስርዓቱ ላይ ሳንካ እየፈጠሩ መሆኑን ጠቁመዋል። የእነዚህ የሽብር ኃይሎች እንቅስቃሴ ከኢትዮጵያ እና እስራኤል ባሻገር ለአውሮፓ፣ አሜሪካ፣ እስያና ለሌሎች ሀገራትም ጭምር የደህንነት ስጋት መሆኑን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ መልስ ማግኘት መሰል የሽብር ኃይሎች እንቅስቃሴን በመግታት የኢኮኖሚና የደኅንነት ሉዓላዊነቷን ለማስጠበቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውም ነው አምባሳደር አብርሃም ንጉሴ (ዶ/ር) ያመላከቱት። በመሆኑም የኢትዮጵያ አስተማማኝ ወደብ የማግኘት ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ተቀባይነት ያለውና እስራኤልም የምትደግፈው መሆኑን ጨምረው አረጋግጠዋል። በተጨማሪም የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነትና ወደ ቀይ ባህር የመመለስ ምክንያታዊ ጥያቄ የምስራቅ አፍሪካ ቀጣናን ሰላምና ደኅንነት ለማስጠበቅ ብሎም ቀጣናውን በመሰረተ ልማትና በኢኮኖሚ ለማስተሳሰር ጉልህ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በየዓመቱ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቀነስ የሚያስችል አቅም እየፈጠረች እንደምትገኝም ገልጸዋል። እስራኤልም በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፎች ያላትን ልምድና ተሞክሮ በማጋራት ድጋፏን እንደምታጠናክር አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ብዝኅ የተፈጥሮ ሃብት፣ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና አምራች የሰው ሃይል ከእስራኤል ቴክኖሎጂና ፈጠራ ትብብር ጋር በማቆራኘት ፈጣን ዕድገት ማስመዝገብ እንደሚያስችላት አንስተዋል። ኢትዮጵያ በዓድዋ ድል ለአፍሪካውያን የነፃነት ምልክት እንደሆነችው ሁሉ፤ ድህነትንና ኋላ ቀርነትን በመግታት እንዲሁም በዲጂታል ሥርዓትና ብዝኅ ልማትም ፋና ወጊ መሆኗን ተናግረዋል።
የአዲስ አበባ ፈጣን የከተማ ለውጥ የሚያስደንቅ ነው - የጀርመኑ ዲፕሎማት
Sep 10, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ እየተከናወኑ ያሉ ሁሉን አቀፍ የከተማ ልማት ስራዎች መዲናዋን በከፍተኛ ፍጥነት እንድትለወጥ ማድረጋቸውን በኢትዮጵያ የጀርመን ተጠባባቂ አምባሳደር ፈርዲናንድ ቮን ዌይሄ ገለጹ። ዘመናዊ ኮሪደሮች፣ መልሰው ያገገሙ የወንዞች ዳርቻዎች፣ የህዝብ መዝናኛ ስፍራዎች እና እየሰፉ ያሉ አረንጓዴ ቦታዎች ለከተማዋ አዲስ መልክ መስጠታቸውን አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። ባለፉት ሶስት ዓመታት በአዲስ አበባ በቆዩባቸው ጊዜያት በከተማዋ የታዩ ለውጦች፣ በተለይም የኮሪደር ልማት ስራዎችንና ለህዝብ መዝናኛ ክፍት ቦታዎችን የማስፋት አጠቃላይ እንቅስቃሴን በቅርብ መከታተላቸውን ተናግረዋል። በቆይታቸው የታዩ ተጨባጭ ለውጦችን መመልከታቸውንም ገልጸዋል። የለውጡ ፍጥነት፣ የስራ ቁርጠኝነት እና ጥንካሬ የሚያስደንቅ መሆኑንም ነው የተናገሩት። በአዲስ አበባ የሚከናወኑ የተለያዩ የልማት ስራዎች እርስ በእርሳቸው የተሳሰሩ እና ሰፊ የከተማ ፕላን እቅድን መሰረት ያደረጉ መሆናቸውን ለመገንዘብ እንደሚቻልም አመልክተዋል። ሁሉም የኮሪደር ስራዎች እና የልማት እንቅስቃሴዎች አንዱ ከሌላው ጋር ተጣጥመውና ተቀናጅተው የሚከናወኑ መሆናቸውም የሚደነቅ ነው ብለዋል። በቀበና ወንዝ አካባቢ፣ ከጀርመን ኤምባሲ አቅራቢያ አንስቶ እስከ ፈረንሳይ ኤምባሲ ድረስ ያሉትን ቦታዎች በመጥቀስ፣ እነዚህ ስፍራዎች የከተማዋ ገጽታ መለወጥ መገለጫዎች መሆናቸውን ጠቁመዋል። ለውጦቹ በግንባታና በመሰረተ ልማት ላይ ብቻ የተወሰኑ እንዳልሆኑም ነው ያነሱት። አሁን ላይ በርካታ ነዋሪዎች ከሰዓት በኋላ ጊዜያቸውን ከቤት ውጭ በማሳለፍ፣ በወንዞች ዳርቻዎች የእግር ጉዞ በማድረግ እና ህጻናትም በአዲሶቹ የብስክሌት መንገዶች እየተጠቀሙ መሆኑ ትልቅ ለውጥ ነው ብለዋል። አምባሳደሩ የአዲስ አበባን የአረንጓዴ ልማት ስራዎች ከኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተሳሰሩ መሆናቸውን ነው ያነሱት። መርሃ ግብሩ የዛፍ ተከላ፣ የደን ልማት እና የአካባቢ ጥበቃን ከሀገሪቱ የልማት አጀንዳዎች ጋር የተቀናጀ መሆኑንም አድንቀዋል። በግላቸው በመቶዎች የሚቆጠሩ ዛፎችን መትከላቸውንም አስታውሰዋል። የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ስኬት የተመሠረተው ዛፍ በመትከል ሂደቱ ላይ ብቻ ሳይሆን፣ ዛፉ እስኪጸድቅና ሙሉ ዕድገት እስኪያሳይ ድረስ በሚደረግ ቀጣይነት ያለው እንክብካቤ ላይ መሆኑን ከራሳቸው ተግባራዊ ልምድ መረዳታቸውን ገልጸዋል። ዛፍ መትከል ብቻ ሳይሆን ዛፉ እያደገ ሲሄድ አብሮ መንከባከብና መከታተልን ይጠይቃል ብለዋል።
በበዓል ገበያ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶች በቂ አቅርቦት በመኖሩ የተረጋጋ ግብይት እያካሄድን ነው -ሸማቾች
Sep 10, 2026 118
ሀዋሳ፣ ጳጉሜን 5/2018 (ኢዜአ):- በሀዋሳ ከተማ ለዘመን መለወጫ የበዓል ገበያ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶች በቂ አቅርቦት በመኖሩ የተረጋጋ ግብይት እያካሄዱ መሆናቸውንሸማቾች ገለጹ ። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር በበኩሉ የአዲስ አመት ዘመን መለወጫ በዓልን ታሳቢ ያደረገ አማራጭ የግብይት ማዕከላትን በማመቻቸት በቂ የምርት አቅርቦት እንዲኖር ማድረጉን አመልክቷል፡፡   ኢዜአ በከተማዋ በተለያዩ አከባቢዎች ተዘዋውሮ እንተደመለከተው የግብርናም ሆነ የኢንዱስትሪ ምርቶች በስፋት የቀረቡ ሲሆን በተመቻቹ አማራጭ የገበያ ማዕከላት ነዋሪዎች የበዓል ግብይታቸውን እያካሄዱ ናቸው።   አስተያየታቸውን ከሰጡት ሸማቾች መካከል ወይዘሮ መቅደስ ካሳሁን አስተዳደሩ ባመቻቸው የአማራጭ ግብይት ማዕከላት በቂ የሆነ የፋብሪካና የኢንደስትሪ ምርት አቅርቦት መኖሩን ጠቅሰዋል።   በገበያው ከመደበኛው የበዓል ቅናሽ ዋጋ በመኖሩ ሸቀጦችን በተረጋጋ ሁኔታ እየተገበያዩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በከተማዋ የግብርናም ሆነ የኢንዱስትሪ ምርቶች በጥሩ ሁኔታ በመቅረባቸው የዋጋ ሁኔታም የተረጋጋ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ሌላው ሸማች አቶ ኢሳያስ ከበደ የተባሉ ናቸው ።   በመደበኛው ገበያና በአማራጭ የግብይት ማዕከላት በማህበራት በኩል ምርቶቻቸውን ማቅረባቸው ሁሉም እንደአቅሙ መሸመት የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። አስተዳደሩ ባመቻቸው የመሸጫ ቦታ ከመደበኛው ገበያ በቅናሽ ለሸማቹ እየሸጡ መሆኑን የተናገረችው ደግሞ ወይዘሪት ብሩክ ቃሬሶ ነች።   የአዲስ ዘመን የበዓል ገበያ የተረጋጋ መሆኑን የተናገሩት የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ አጋና ነቶ ለዚህም የተደረጉ ቅድመ ዝግጅቶች የላቀ ሚና መጫወታቸውን ተናግረዋል። የበዓል ገበያውን የተረጋጋ ለማድረግ በምርት አቅርቦትና የዋጋ ቁጥጥርና ክትትል የሚያደርግ ከሰባት ተቋማትና የተለያዩ አካላት ያሉበት ግብረ ሀይል ተቋቁሞ ሲሰራ መቆየቱን ገልጸዋል።   በተለይም የምርት እጥረት እንዳይከሰት ከመደበኛ ገበያዎች በተጨማሪ አማራጭ የግብይት ማዕከላትን በማደራጀት አምራቹና ሸማቹ በቀጥታ የሚገናኙበት ሁኔታ በማመቻቸት ማህበረሰቡ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ መደረጉን ተናግዋል። የክትትልና ቁጥጥር ስርዓቱም በቅንጅት እየተሰራ እና በአጠቃላይ የበዓል ገበያ የተረጋጋ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡      
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም