ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ሪፎርም የቻይና ባለሀብቶችን ይበልጥ እየሳበ ነው-አምባሳደር ቼን ሃይ
Aug 26, 2026 255
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና እየተሻሻለ የመጣው የኢንቨስትመንት ከባቢ ይበልጥ የቻይና ባለሀብቶችን እየሳበ እንደሚገኝ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ ገለጹ። አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ግዙፍና ፈጣን እድገት ካላቸው ኢኮኖሚዎች አንዷ መሆኗን ገልጸዋል። ሀገሪቱ ለዓለም አቀፍ የንግድ አጋሮችና ባለሀብቶች ሰፊ የኢንቨስትመንት እድሎችን እያቀረበች እንደምትገኝም አመልክተዋል። አምባሳደሩ የኢንዱስትሪ ልማት፣ የከተሜነት መስፋፋት እና የግብርና ዘመናዊነት አሰራሮችን ጨምሮ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ቁልፍ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽን ዘርፎች እየተመዘገቡ ያሉ ውጤቶችን አድንቀዋል። በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው እያደገ የመጣው የኢኮኖሚ ትስስር ለሀገራዊ ዕድገት አስተዋጽኦ ከማበርከት ባለፈ፣ የማህበረሰቡ ኑሮ እንዲሻሻል መልካም አጋጣሚ መፍጠሩን አንስተዋል። ቻይናና ኢትዮጵያ ሀገራዊ ዕድገትና የመዘመን ራዕይን እውን ለማድረግ የጋራ የሆነ መሻት እንዳላቸውም አብራርተዋል። አምባሳደሩ ባለፉት ሁለት ዓመታት በኢትዮጵያ በቆዩበት ጊዜ በሀገሪቱ የኢኮኖሚ ምህዳርና የንግድ ከባቢ ላይ ግልጽ ለውጦች እንደተመለከቱም ተናግረዋል። በዚህም የቻይና ባለሀብቶችና ሥራ ፈጣሪዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ጠቅሰው፣ አዳዲስ ፋብሪካዎችና ማምረቻዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን አንስተዋል። የኢንቨስትመንት ከባቢው እንዲሻሻል በፌዴራልና በክልል መንግሥታት የተደረጉ ማሻሻያዎች ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑን የገለጹት አምባሳደሩ፣ እነዚህ እርምጃዎች ለንግድና ለኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር እንዳስቻሉም አክለዋል። በተጨማሪም በኢትዮጵያና በቻይና መካከል ያለው የንግድ ግንኙነት እየሰፋ መሄዱን፣ በተለይም የቻይና ሸማቾች ለኢትዮጵያ ምርቶች ያላቸው ፍላጎት እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል። እንደ ቡናና ሰሊጥ ያሉ የኢትዮጵያ የግብርና ምርቶች በቻይና ገበያ ያላቸው ተወዳጅነት ማደጉን ጠቅሰው፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የኢንዱስትሪና እሴት የተጨመረባቸው ምርቶችም ጭምር በቻይናውያን ሸማቾች ዘንድ ሰፊ ተቀባይነት እያገኙ መምጣታቸውን አመልክተዋል። አምባሳደሩ በቻይና ንግድ ተቋማትና በኢትዮጵያ መንግሥት አካላት መካከል በቀጣይ የሚኖረው ትብብር የሀገሪቱን የንግድ ምህዳር ይበልጥ እንደሚያጠናክረውና ለንግድና ኢንቨስትመንት ሰፊ ዕድሎችን እንደሚፈጥር ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። የንግድና ኢንቨስትመንት ጠንካራ ትብብር የሁለቱን ሀገራት ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከማፋጠን ባለፈ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ይበልጥ እንደሚያጎለብተውም ተናግረዋል። የኢትዮጵያና የቻይና ግንኙነት በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂክ አጋርነት (all-weather strategic partnership) ደረጃ ከፍ ማለት፣ የሁለቱን ሀገራት ለሰፊ ትብብርና ለጋራ ልማት ያላቸውን ቁርጠኝነት የሚያሳይና የቻይና-አፍሪካን የኢኮኖሚ ግንኙነት አጠቃላይ ፋይዳ አጉልቶ የሚያሳይ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በሰሜን ጎንደር ዞን 29 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በስንዴ ሰብል ለምቷል
Aug 26, 2026 329
ጎንደር ፤ነሐሴ 20 /2018 (ኢዜአ)፡- በሰሜን ጎንደር ዞን በያዝነው ክረምት 29 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን መሬትን በስንዴ ሰብል መሸፈን መቻሉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ፋሲካ መርሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የስንዴ ልማቱን በማስፋት ለኢንዱስትሪዎች ግብዓትና ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት እየተቻለ ነው፡ በ2018/19 የመኸር ምርት ዘመንም 35 ሺህ 290 ሄክታር መሬት በስንዴ ሰብል በማልማት ከአንድ ነጥብ አንድ ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን ገልጸዋል። እስካሁን በተደረገ ጥረትም 29 ሺህ 439 ሄክታር መሬት በዘር በመሸፈን የአረምና የተባይ መከላከል ተግባር እየተከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። አርሶ አደሩ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ማዳበሪያ እንዲሁም ምርጥ ዘር በአግባቡ እንዲጠቀም በማድረግ፣ ምርታማነቱን በሄክታር በአማካይ 31 ኩንታል ለማድረስ እየተሠራ መሆኑንም አስረድተዋል። በተጨማሪም በመካናይዜሽን በመታገዝ በኩታ ገጠምና በመስመር አሠራር በመዝራት የታቀደውን ምርት ለመሰብሰብ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል። የዘር ሥራው አሁንም ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቁመው፤ ይህም የታቀደውን መሬት ሙሉ በሙሉ ለማልማት የሚያስችል መሆኑን አስገንዝበዋል። በዞኑ በተያዘው የመኸር ምርት ዘመን በአጠቃላይ ከ156 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት 4 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማምረት እየተሠራ እንደሚገኝ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በጋምቤላ ክልል የልማት አቅሞችን ለይቶ ተግባራዊ የማድረግ ስራ ቀዳሚ ትኩረት ይሰጠዋል-ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ
Aug 26, 2026 91
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 20/ 2018 (ኢዜአ) ፡-የጋምቤላ ክልል ሕዝብን የኑሮ ደረጃ በዘላቂነት ለማሻሻል በየዘርፉ ያሉ የልማት አቅሞችን አውጥቶ ተግባራዊ የማድረግ ስራ ቀዳሚ ትኩረት እንደሚሰጠው ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። የቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት በጋምቤላ ክልል በሚገኙ ዘጠኝ ወረዳዎች በአዲሱ በጀት ዓመት ለሚያስፈጽማቸው የልማት ስራዎች የሚሆን ከ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት በክልሉ ስቲሪንግ ኮሚቴ አጽድቋል።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ ወደ ክልሉ የሚመጡ አጋዥ የልማት ፕሮጀክቶችን ከልማት እቅዶች ጋር አጣጥሞ በመተግበር የህዝቡን ህይወት ለመለወጥ በትኩረት መስራት ይገባል። በክልሉ እየተተገበረ ያለው የቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት ባለፉት ዓመታት ባከናወናቸው የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎች ህዝቡን ተጠቃሚ ማድረጉንም ገልጸዋል። አክለውም በዘንድሮው በጀት ዓመት በትምህርት፣ በግብርና፣ በመንገድና በሌሎች የኑሮ ማሻሻያ ዘርፎች የታቀዱት ስራዎች የህዝቡን ህይወት ሊያሻሽሉ የሚችሉ መሆናቸውን አስገንዝበዋል። ለፕሮጀክቶቹ ስኬታማነት የስትሪንግ ኮሚቴውና የሌሎች ባለድርሻ አካላት ድጋፍ፣ ትብብርና ቅንጅታዊ አሰራር ሊጎለብት እንደሚገባ አመልክተው ለዚህም የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና ትብብር እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የፕሮጀክቱ የጋምቤላ ክልል አስተባባሪ ዶክተር ቤል ቢቾክ በበኩላቸው፣ ፕሮጀክቱ ባለፉት ዓመታት የማህበረሰቡን ኑሮ የሚለውጡ ስራዎችን ሲያከናውን መቆየቱን ገልፀዋል። በዘንድሮው በጀት ዓመትም ተመሳሳይ ተግባራትን ለማከናወን ከ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ በመመደብ ወደ ተግባር ምዕራፍ መግባቱን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ 35 የትምህርት ቤት፣ የእንስሳት ጤና ኬላ፣ የመንገድ ግንባታና ዲዛይን እንዲሁም ሌሎች የህዝቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ ፕሮጀክቶች እንደሚከናወኑ ጠቁመዋል። ለእነዚሁ ተግባራት ስኬትም የባለድርሻ አካላትን ድጋፍና ትብብር እንደሚያስፈለግ ነው የተናገሩት። የቆላማ አካባቢ የኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት በመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ስር በሰባት ክልሎችና በአንድ ከተማ አስተዳደር በሚገኙ 120 ወረዳዎች የማህበረሰቡን ኑሮ ለማሻሻል እየተተገበረ የሚገኝ መሆኑ መረጃ ያመለክታሉ ።
በድሬዳዋ አስተዳደር ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ ልማትን ለማቀላጠፍ ቅንጅታዊ ሥራ ተግባራዊ ተደርጓል
Aug 26, 2026 99
ድሬዳዋ፣ነሐሴ 20/2018(ኢዜአ)፡-በድሬዳዋ አስተዳደር ገቢን በአግባቡ ሰብስቦ ልማትን ለማቀላጠፍ ቅንጅታዊ ሥራ ተግባራዊ መደረጉን የአስተዳደሩ ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አብዱልሰላም መሐመድ (ዶ/ር) ተናገሩ ። በዘንድሮ በጀት ዓመት በአስተዳደሩ 15 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ቅንጅታዊ እንቅስቃሴዎች መጀመራቸው ተመላክቷል።   የድሬዳዋ ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አብዱልሰላም መሐመድ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ አስተዳደሩ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢን በአግባቡ ለመሰብሰብ የግብር ከፋዮችን ግንዛቤ ከማሳደግ ባለፈ በቴክኖሎጂ ታግዘው ግብራቸውን በመክፈል ግዜና ገንዘባቸውን እንዲቆጥቡ እያደረገ ነው። የከተማዋ ኢኮኖሚ የሚያመነጨውን ገቢ በአግባቡ በመሰብሰብ የነዋሪዎችን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ገቢዎች እንዲሁም ከማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች 15 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ሥራው ተጀምሯል ብለዋል። ስራውንም በንቅናቄ በመምራት ሐምሌ ወር ብቻ ከ934 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ከ890 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡን ጠቁመዋል። በእዚህም የዕቅዱን ከ95 በመቶ በላይ ለማሳካት እንደተቻለና ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከ685 ሚሊዮን ብር በላይ ብልጫ እንዳለው አመልክተዋል። በሚሰበሰብ ገቢም የህዝብ የመንገድ፣ የንፁህ መጠጥ ውሃ፣ የአነስተኛ መስኖ አውታሮች፣ የኮሪደር ልማት እና ሌሎች የመሠረተ ልማት ሥራዎችን በማስፋፋት የነዋሪውን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ይሰራል ብለዋል።   በድሬዳዋ ገቢዎች ባለስልጣን ግብራቸውን በመክፈል ላይ ከነበሩት መካከል ወይዘሮ ሂዩስቲና ስዩም እና አቶ ዮሴፍ አለባቸው ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በባለስልጣኑ የተዘረጋው ቀልጣፋ አገልግሎት ግብራቸውን በወቅቱ ለመክፈል አግዟቸዋል።   የሚከፍሉት ግብር ለድሬዳዋ ዕድገት እና ለነዋሪው ተጠቃሚነት እንደሚውል በማመን ግብራቸውን በወቅቱና በታማኝነት መክፈላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።
ለአዲስ አበባ ተጨባጭ እድገት በቅንነትና በታማኝነት መስራታችንን እንቀጥላለን- ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Aug 26, 2026 183
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፦ ለአዲስ አበባ ከተማ ተጨባጭ እድገት በቅንነት እንዲሁም በታማኝነት መስራታችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ የመዲናዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባዋ የዘመነ መሰረተ ልማት፤ የዘመነ አገልግሎት ለዘመናዊ ከተማ! በሚል ባስተላለፉት መልዕክት፤ በከተማዋ አራት ዘመናዊ የተሽከርካሪ ማቆሚያዎች፣ ተርሚናሎችና ገበያ ማዕከላት (በጎተራ፥ ቦሌ፣ የካ እና ቀበና) ዛሬ መርቀው አገልግሎት ማስጀመራቸውን ጠቁመዋል። እነዚህ መሰረተ ልማቶች የትራፊክ መጨናነቅን የሚያቃልሉ፣ የትራንስፖርት ሥርዓትን የሚያሻሽሉ፣ ህዝባችንን ከዝናብና ፀሐይ እንግልት የሚከላከሉ፣ በርካታ የስራ እድሎችን የሚፈጥሩ ምቹ ፣ ንፁህ እና የሰውን ክብር የሚመጥኑ የዘመነ አገልግሎት የሚሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።   መሰረተ ልማቶቹ በአንድ ጊዜ በርካታ ተሽከርካሪዎችን የማስተናገድ ዓቅም ያላቸው ዘመናዊ የተሽከርካሪ ማቆሚያዎች፣ የታክሲ እና የአውቶቡስ ተርሚናሎች፣ የአየር ብክለትን የሚከላከሉ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ ማድረጊያዎች፣ ሰፊ የህዝብ መዝናኛ ስፍራዎች፣ የንግድ ሱቆች፣ ካፍቴሪያና ሬስቶራንቶች እና የልጆች መጫወቻና ማረፊያ ስፍራዎች የተሟሉላቸው ናቸው። በተጨማሪም ምቹ የተሳፋሪ መጠበቂያ ስፍራዎች፣ የአስተዳደር እና የትኬት መቁረጫ ቴክኖሎጂዎች፣ አሳንሰሮች እና ንፁህ መፀዳጃ ቤቶች እንዲሁም የደህንነትና የአደጋ ቅድመ መከላከል ሥርዓቶች የተሟሉላቸው ሆነው የኢኮኖሚና የማህበራዊ አገልግሎትን ለማሳለጥ ትልቅ አስተዋጽዖ የሚያበረክቱ እንደሆኑም ከንቲባዋ ተናግረዋል። ከለውጡ በፊት ሶስት ሺህ ብቻ የነበረውን የአንድ ጊዜ የተሽከርካሪ ማቆሚያ አቅም እና ምንም ያልነበረንን ተርሚናል በአሁኑ ጊዜ በጥራትና በፍጥነት የተገነቡ፣ ዘመናዊ የተሽከርካሪ ማቆሚያዎችን እና ተርሚናሎችን ከ170 ሺህ በላይ ማድረስ መቻሉን አመልክተዋል። ለከተማችን ነዋሪዎች ተጠቃሚነት በተጨባጭ ቃላችንን በተግባር ስራዎችን እየፈጸምን በቅንነትና በታማኝነት እየሰራን እንገኛለን። አዲስ አበባ ከዚህ በላይ ይገባታል ቀጣይም ከሰራነው በላይ እንተጋለን! ብለዋል። ከንቲባዋ የዛሬዎቹ ፕሮጀክቶች እውን እንዲሆኑ ለተጉ፣ ላስተባበሩ የዲዛይንና ግንባታ ስራዎች ቢሮ አመራሮችና ሰራተኞች፣ የትራንስፖርት ቢሮ አመራሮች፣ ኮንትራክተሮች፣ አማካሪዎች በዚህ ስራ ለተሳተፉ በሙሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ከከተማዋ የዕድገት ፍጥነት ጋር የሚመጣጠን የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ማከናወን ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Aug 26, 2026 141
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፦ ከመዲናዋ የዕድገት ፍጥነት ጋር የሚመጣጠን የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ማከናወን የከተማ አስተዳደሩ ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የተገነቡ የተቀናጁ የትራንስፖርት ተርሚናሎች፣ የመኪና ማቆሚያዎችና የገበያ ማዕከላትን መርቀው ስራ አስጀምረዋል።   በምረቃ መርሃ ግብሩ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ቡዜና አልከድር፣ በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ከተማ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይን እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዲዛይንና ግንባታ ሥራዎች ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር አያልነሽ ሐብተማሪያምን ጨምሮ ሌሎች የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፣ ከከተማዋ የዕድገት ፍጥነት ጋር የሚመጣጠን የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን ማከናወን የከተማ አስተዳደሩ ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫ ነው። ዛሬ የተመረቁት መሰረተ ልማቶችም በከተማዋ የትራንስፖርት አገልግሎትን ለማዘመንና የትራፊክ መጨናነቅን ለመቅረፍ አይነተኛ ሚና ይኖራቸዋል ብለዋል። አዲሶቹ የትራንስፖርት ተርሚናሎችና የመኪና ማቆሚያዎች የከተማዋን የትራፊክ ፍሰት ለማቃለል እንዲሁም ምቹ የእግረኛ መንገዶችን ለመፍጠር ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ገልጸዋል።   መሰረተ ልማቶቹ መንገድ ዳር የሚቆሙ ተሽከርካሪዎችን በማስቀረት የከተማዋን የትራፊክ መጨናነቅ እንደሚቀንስም ከንቲባዋ አመላክተዋል። በመኪና ማቆሚያዎቹና ተርሚናሎቹ ውስጥ የዲጂታል ክፍያና የደህንነት ካሜራዎችን ጨምሮ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች መገጠማቸውን ጨምረው አስታውቀዋል። ፕሮጀክቶቹ በተያዘላቸው ጊዜና ጥራት ተጠናቅቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ ሚናቸውን የተወጡ አካላትን አመስግነው ህብረተሰቡም የተገነቡ ዘመናዊ የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶችን በአግባቡ እንዲጠቀም አስገንዝበዋል።   የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶቹ የተገነቡት በቦሌ ኖክ፣ በየካ፣ በቀበና እና በጎተራ ሲሆን በውስጣቸው የገበያ ማዕከላትን ጭምር ያካተቱ ናቸው።
በሀዋሳ የሐይቅ ዳርቻ እና የኮሪደር ልማት ሥራዎችን በተያዘው ጊዜ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ ነው-ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Aug 26, 2026 189
ሀዋሳ፣ ነሐሴ20/2018 (ኢዜአ)፡-በሀዋሳ ከተማ የተጀመሩ የሐይቅ ዳርቻ እና የኮሪደር ልማት ሥራዎችን በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ፡፡ ሀዋሳ ከተማን ሳቢ፣ ምቹና ይበልጥ ተመራጭ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች በርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ እና በሌሎች የሥራ ሃላፊዎች ተጎብኝቷል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት ከተማዋ ያላት የተፈጥሮ ውበት ይበልጥ ጎልቶ እንዲወጣ የኮሪደር ልማት ሥራው ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል። በአሁኑ ወቅት ግንባታው እየተካሄደ ያለው የሐይቅ ዳርቻ እና የኮሪደር ልማት ሥራዎች ከተማዋን ይበልጥ ለኑሮ፣ ለኢንቨስትመንት፣ ለመዝናኛነት እና ለኮንፈረንስ ምቹና ተመራጭ እንደሚያደርጋት ጠቁመዋል።   እነዚህ የልማት ሥራዎች በተያዘላቸው የጊዜ ገደብ ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ የክልሉ መንግስት መላውን ህዝብ በማስተባበር አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።   የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው በከተማዋ ለአራተኛ ዙር እየከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ሥራ ከጥቃቅን ሥራዎች በስተቀር ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ መጠናቀቁን አስታውቀዋል። የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ሥራም በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ በቀን ለ24 ሰዓታት እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ለሐይቅ ዳርቻ ልማቱ ህዝቡን በማስተባበር እስካሁን ድረስ 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ መቻሉንም ተናግረዋል። በልማት ሥራዎች ጉብኝት ላይ የሲዳማ ክልልና የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።  
በሐረሪ ክልል በኢንቨስትመንት ዘርፍ የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ውጤታማ እያደረገን ነው -ባለሀብቶችና ወጣቶች
Aug 26, 2026 116
ሀረር፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በሐረሪ ክልል በኢንቨስትመንት ዘርፍ የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ውጤታማ እያደረጋቸው መሆኑን ባለሀብቶችና ወጣቶች ገለጹ። በክልሉ ያለው የኢንቨስትመንት አማራጭ ከከፍተኛ ትምህርት ለተመረቁ ወጣቶች የስራ እድል እየፈጠረ መሆኑ ተመላክቷል። ባለሀብቶችም የክልሉ መንግስት የኢንቨስትመንት ዘርፉን ለማበረታታት በሚያከናውነው ተግባራት በዘርፉ ውጤታማ እያደረጋቸው መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። በሀረር ከተማ በኢንቨስትመንት ከተሰማሩ ባለሀብቶች መካከል የሀምዲ ሜዲካል ሰርጂካል ሴንተር ባለቤትና ስራ አስኪያጅ ዶክተር ኑረዲን አህመድ እንደገለጹት የክልሉ መንግስት መሬት ከመስጠት ጀምሮ የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ ለኢንቨስትመንት ስራቸው ምቹ ሁኔታን ፈጥሮላቸዋል። አሁን ላይ የግንባታ ስራቸውን ከ90 በመቶ በላይ ማጠናቀቃቸውን ጠቁመው በቀጣይ ስድስት ወራት ወደ ተሟላ ስራ እንደሚገቡ አመላክተዋል። በግንባታው ለበርካታ ሰዎች የስራ እድል መፈጠሩን ተናግረዋል። የክልሉ ኢንቨስትመንት ቢሮ እያደረገላቸው ባለው ድጋፍ ግንባታውን በፍጥነት እያጠናቀቁ መሆናቸውን ገልጸዋል ። በሐረር ከተማ በሆቴልና ቱሪዝም ዘርፍ ኢንቨስትመንት ላይ መሰማራታቸውን የገለጸው ደግሞ በከተማው የሐረር ፓላስ ሆቴል ስራ አስኪያጅ ወጣት ሔኖክ ተስፋዬ ነው። የክልሉ መንግስት ከግንባታ ጀምሮ እስካሁን አስፈላጊውን ድጋፍ ሲያደርግላቸው በመቆየቱ ግንባታውን በፍጥነት አጠናቀው ወደ ስራ በመግባት ውጤታማ መሆናቸውን ገልጿል።   ከደብረብርሃን ዩኒቨርሲቲ በመካኒካል ምህንድስና የተመረቀው ወጣት ይስሃቅ ደሳለኝ በክልሉ በኢንቨስትመንት ዘርፍ የሚካሄዱ ግንባታዎች ለተመራቂ ተማሪዎች የስራ እድል እየፈጠሩ መሆናቸውን ተናግሯል።   በክልሉ በግንባታ ላይ በሚገኘው የዘይት ፋብሪካ በተመቻቸለት የስራ እድል አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችና አሰራሮች ጋር በመተዋወቅ እውቀቱን እያዳበረ መሆኑን ገልጿል። የሐረሪ ክልል ኢንተርፕራይዝ ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ምክትል ሃላፊ ሀምዲ ሰለሃዲን እንደገለጹት ባለፉት ዓመታት በክልሉ የኢንቨስትመንት ልማት ላይ የተከናወኑ ተግባራት አበረታችና መነቃቃትን የፈጠሩ ናቸው።   ባለፉት አምስት ዓመታት ከ20 ቢሊየን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ባለሃብቶች በኢንቨስትመንት ዘርፍ ፈቃድ መውሰዳቸውን ተናግረዋል። የክልሉ መንግስት ለኢንቨስትመንት ዘርፉ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው ወደ ኢንቨስትመንት የገቡ ባለሀብቶችም ወደ ምርትና አገልግሎት እንዲገቡ እየተደረገ ያለው ክትትልና ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠሉን አስታውቀዋል።    
ኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ ሽግግርን ውጤታማ በማድረግ በኩል ለአፍሪካ ሀገራት ተምሳሌት የሆነ ተግባር አከናውናለች
Aug 26, 2026 129
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በግብርና ዘርፍ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እያከናወነች ባለችው ተግባራት ለአፍሪካ ሀገራት ተምሳሌት መሆኗን የአህጉር አቀፍ ተቋማት የስራ ሀላፊዎች እና ባለሙያዎች ገለጹ። በአፍሪካ ህብረት ልማት ኤጀንሲ የግብርና እና የገጠር ትራንስፎርሜሽን ዋና ፕሮግራም ባለሙያ ክሌመንት አድጆርሎሎ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የአፍሪካ ሀገራት የምግብ ስርዓታቸውን ለማጠናከርና ፍላጎታቸውን በራስ አቅም ለማሟላት በትብብር ሊሰሩ ይገባል። በአህጉሪቱ እያደገ የመጣውን የህዝብ ፍላጎት በራስ አቅም ለማሟላትና ጠንካራ የምግብ ስርዓትን ለመገንባት ከኢትዮጵያ ተሞክሮ መውሰድ እንደሚገባ ተናግረዋል። የግብርና ምርትና ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ የንግድ ስርዓትንና አጠቃላይ የግብርና ዘርፍ የእሴት ሰንሰለቱን ማጠናከር እንደሚገባም ገልፀዋል። በምግብ ራስን ለመቻልና ምርታማነትን ለማሳደግ የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ብሎም በለውጥ ሂደት ላይ ተሳታፊ የሚያደርጉ ስራዎች ወሳኝ መሆናቸውን አስረድተዋል። ኢትዮጵያ በዘርፉ ያከናወነቻቸውን ተግባራት እና ያስመዘገበቻቸውን ውጤቶች ሌሎች ሀገራት ሊጋሩት እንደሚገቡም አክለዋል። ኢትዮጵያ ስንዴን በስፋት በማምረት የሀገር ውስጥ ፍጆታ ከማሟላት በተጨማሪ ለውጭ ገበያ ማቅረብ መጀመሯ የሀገር ውስጥ የግብርና ምርትን ማሳደግ ያለውን አስተዋፅኦ ያመላክታል ብለዋል። ኢትዮጵያን በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር የግብርና እና የምግብ ስርዓትን ከአካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም የሚያስችል ተግባርን በማስተሳሰር የሚደረግ ውጤታማ ተግባር ማሳያ ነው ሲሉም ገልጸዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርግና ለአህጉር አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎች አስተዋጽኦ እያበረከተ የሚገኝ መሆኑንም ጠቁመዋል። በአጀንዳ 2063 የቀጣናዊ ስትራቴጂክ ትንተናና እውቀት ድጋፍ ሰጪ ስርዓት ዲፓርትመንት ኃላፊ ፖል ጉቲጋ የኢትዮጵያ የግብርና ሽግግር ለቀጣናው ሀገራት ትምህርት የሚሆን ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ፣የኢንዱስትሪ ዘርፉን ለማጠናከርና የአርሶ አደሮችን ገቢ ለማሳደግ ያከናወናቸው ውጤታማ ተግባራት የአፍሪካ ሀገራት ሊወስዷቸው የሚገቡ ተሞክሮዎች መሆናቸውንም ጠቁመዋል። በኢትዮጵያ መንግስት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት አስደናቂ እንደሆኑም ነው የገለጹት።
በክልሉ የተጀመሩ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች በአዲሱ በጀት አመትም ይበልጥ ተጠናክረው ይቀጥላሉ- ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Aug 26, 2026 258
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፡-የህዝቡን ጥያቄዎች መሰረት በማድረግ የተጀመሩ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች በአዲሱ በጀት አመትም ይበልጥ ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን የአማራ ክልል ርእሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። የአማራ ክልል የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ እና የ2019 ዕቅድ የትውውቅ መድረክ በባሕር ዳር ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል።   በመድረኩ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ፈተናዎችን በማለፍና ችግሮችን ወደ እድል በመቀየር ጭምር በሁሉም ሴክተሮች አበረታች የሆኑ ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል። በተለይም የ25 ዓመት አሻጋሪ የልማት እና የ5 ዓመት ስትራቴጂካዊ ዕቅዶችን ለመተግበር የተደረገው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን አንስተው በሁሉም ዘርፍ የሕዝብን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ስኬታማ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል። የተቋማትን፣ የአመራሩንና የባለሙያውን የመፈጸም አቅም በማሳደግ የተሻለና ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ በመገንባት በኩል ተስፋ የሚሰጡ ጅምሮች መኖራቸውንም አንስተዋል። በመሆኑም የክልሉን ህዝብ ጥያቄ መሰረት በማድረግ የተጀመሩ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች በአዲሱ በጀት አመትም ይበልጥ ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን ተናግረዋል።   በአዲሱ ዓመት አዲስ መንግስት የሚመሰረትበትና ተስፋ የተሰነቀባቸው የልማት ስራዎችም በላቀ ቁርጠኝነት የሚተገበሩበት ይሆናል ብለዋል። በተጨማሪም በየደረጃው በቴክኖሎጂ የታገዘ ዘመናዊ አሠራርን ተግባራዊ በማድረግ ሕዝብን የሚያረካ አገልግሎት ተደራሽ ማድረግ ላይ ትኩረት ይደረጋል ብለዋል። ከቀደሙ ተግዳሮቶች ትምህርት በመውሰድና የተሻሉ ተሞክሮዎችን በማስፋት በአዲሱ በጀት ዓመት የሕዝብን ደኅንነት በአስተማማኝ ሁኔታ የመጠበቅና ዘርፈ-ብዙ ምርታማነትን የማሳደግ ሥራ በትኩረት እንደሚሠራ ገልጸዋል። የክልሉን ብሎም የሀገርን ኢኮኖሚ በዘላቂነት በሚያሳድጉ ተግባራት ላይ በማተኮር ለስኬታማነቱ የተቀናጀ ጥረት የሚደረግ መሆኑንም ተናግረዋል። በመሆኑም በየደረጃው ያለው አመራር የጋራ ራዕይ ሰንቆና በተግባራት ዙሪያ ጠንካራ ተግባቦት በመፍጠር በተሻለ ቁርጠኝነት እና በጊዜ የለኝም መንፈስ መስራት እንዳለበት አሳስበዋል። ለሁለት ቀናት በሚካሄደው የምክክር መድረክ የክልሉ የተለያዩ ተቋማት አመራሮችና ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።  
የመገጭ ግድብ የመደመር መንግስት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅም ማሳያ ነው
Aug 25, 2026 311
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦የመገጭ ግድብ የመደመር መንግስት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅም ማሳያ መሆኑን የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ገለጹ። የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የመገጭ ግድብ ግንባታ ያለበትን ደረጃ ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ተቋማት ለተውጣጡ ጋዜጠኞች አስጎብኝቷል። የጎንደር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ጉብኝቱን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፤የመገጭ ግድብ የጎንደር ከተማ የዘመናት ጥያቄ መሆኑን ገልጸዋል። የመገጭ ግድብ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ለሕዝቡ ያልተሠራውን ተሠራ እየተባለ 18 ዓመታትን ማስቆጠሩን ጠቅሰዋል። መገጭ ለንጹህ መጠጥ ውሃና ለመስኖ ልማት በመዋል ለኢትዮጵያ ብዙ ጥቅም ማስገኘት የሚችል ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። ይሁን እንጂ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር ሰጭነት ፕሮጀክቱን እንደገና በማጥናት ሕዝብ ከባዶ ተስፋ ወደሚጨበጥ ሕልም ማምጣት እንደተቻለ ገልጸዋል። ይህም ለሕዝቡ ከሚሰጠው ቀጥተኛ ጥቅም ባለፈ፣ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት እንዳለው በተግባር ገልጧል ብለዋል። በመገጭ ግድብ ግንባታ የታየው ፈጣን የግንባታ ለውጥ የመደመር መንግሥት ፕሮጀክት ጀምሮ በፍጥነት የማጠናቀቅ አቅሙን በተግባር ያሳየበት መሆኑን ገልጸዋል። የመገጭ ግድብ ሰፊ የእርሻ መሬት ላለው የደንቢያ አካባቢ የልማት ተስፋ፤ ለጎንደር ከተማ ደግሞ የዘላቂ ንጹህ መጠጥ ውሃ ብስራት ይሆናል ብለዋል። ሕብረተሰቡ የግድቡን አስፈላጊነት በወጉ በመረዳት አካባቢውን በንቃት እየጠበቀ፣ የፕሮጀክቱን አፈጻጸም በቅርበት እየተከታተለው መሆኑን ገልጸዋል። ለ18 ዓመታት ሕዝቡን በባዶ ተስፋና በጎርፍ ሲያማርር የነበረው የመገጭ ግድብ፣ ሁለት ዓመት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግንባታው ተጠናቆ በቅርቡ ይጠናቀቃል ብለዋል።  
የአፍሪካን የጤና ሥርዓት በራስ አቅም ለማዘመን የአባል ሀገራትን ትብብር ማጠናከር አስፈላጊ ነው
Aug 25, 2026 221
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካን የጤና ሥርዓት በራስ አቅም ለማዘመን ኢንቨስትመንትንና የአባል ሀገራትን ትብብር ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር መሐመድ ያኩብ ጃናቢ ገለጹ። 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባኤ በአዲስ አበባ ዓድዋ ድል መታሰቢያ እየተካሄደ ይገኛል። የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር መሀመድ ያኩብ ጃናቢ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ 76ኛ የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባኤ በአንድ መድረክ ከመወያየት በላይ ነው። መድረኩ የአፍሪካ የጤና ችግሮች ላይ የጋራ ውይይት በማድረግ የጋራ የመፍትሔ ሀሳብ የሚፈልቅበት መሆኑን ገልጸዋል። በአፍሪካ በመሪዎች ቁርጠኝነት፣ በጤና ተቋማትና ባለሙያዎች ዝግጅት እንዲሁም በማህበረሰቡ ትብብር በጤና ስርዓቱ ላይ መሻሻል ታይቷል ብለዋል። አፍሪካ ከ1 ነጥብ 5 ቢሊየን በላይ ህዝብ ምድር መሆኗን በማንሳትም፤ አፍሪካ የጤና ስርዓቷን በራሷ አቅም ለመገንባት ጠንካራና ቀጣይነት ያለው የጤና ተቋማትን መገንባት ይገባታል ነው ያሉት። በአፍሪካ ለተመዘገበው የጤና አገልግሎት መሻሻል የዓለም ጤና ድርጅት ያልተቋረጠ ድጋፍ ማድረጉን በመግለፅ፤ የአፍሪካ የጤና ኢንቨስትመንትን በራስ አቅም መፍጠር አስፈላጊ ነው። የአፍሪካ ራዕይ ግልጽ ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የጤና ልህቀት ማዕከል መገንባትና የጤና ስርዓቷን በራሷ አቅም መገንባት መሆኑን በመግለጽ። አህጉሪቱ የዕወቀትና የተፈጥሮ ሀብት ችግር የለባትም፤ መሰረታዊው ጉዳይ ተደራሽነትን ማስፋት የሚያስችል የጤና አገልግሎት መስጠት ነው ሲሉም ገልጸዋል። የጤና ሥርዓት ዝማኔ አመራር፣ ኢንቨስትመንትና ትብብር እንደሚጠይቅ ጠቁመውም፤ የዓለም ጤና ድርጅት አፍሪካ አቅሟን እንድትገነባ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።  
የመገጭ ግድብ ግንባታ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ ደርሷል
Aug 25, 2026 161
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ጎንደር ከተማ አቅራቢያ እየተገነባ የሚገኘው የመገጭ ግድብ ፕሮጀክት ግንባታ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ መድረሱን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ የመገጭ የግድብ ግንባታ ያለበትን ደረጃ ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ለተውጣጡ ጋዜጠኞች አስጎብኝቷል። ሚኒስቴሩ የኢትዮጵያን በምግብ ራስን የመቻል ጉዞ የሚያሳኩ የመስኖ ልማት መሰረተ ልማቶችን እያስፋፋ ይገኛል። ከእነዚህ መሰረተ ልማቶች መካከል በአማራ ክልል ጎንደር አቅራቢያ እየተገነባ የሚገኘው መገጭ ግድብ አንዱ ሲሆን ግድቡ ከተጀመረ ረዘም ያለ ጊዜ አስቆጥሯል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ግድቡ በፍጥነት ተጠናቆ አገልግሎት እንዲሰጥ ባስቀመጡት አቅጣጫ መሰረትም በተለይ ባለፉት ሁለት ዓመታት ግድቡን ለማጠናቀቅ በተደረገው ርብርብ አሁን ላይ ወደ ማጠናቀቂያ ምዕራፍ ደርሷል። በመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር የመስኖ ፕሮጀክቶች ፕሮግራም ጽህፈት ቤት ስራ አስኪያጅ እንጂነር አሸናፊ ሊካሳ በሰጡት ማብራሪያ ግንባታው በመጓተቱ ምክንያት ግንባታውን ይዞ የነበረው ተቋራጭ በአዲስ እንዲተካ መደረጉን አንስተዋል። አሁን ላይም ግድቡን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ ሁሉን አቀፍ ርብርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። የውሃ መስኖ መቆጣጠሪያው ሲቪል ስራ ሙሉ በሙሉ መጠናቀቁን ጠቁመው፤ የኤሌክትሮ መካኒካል ስራው በሂደት ላይ መሆኑን ገልጸዋል። ግድቡ በአሁኑ ወቅት ውሃ መያዝ መጀመሩን ጠቅሰው፤ እስካሁን 33 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃ መያዙንም ተናግረዋል። የግድቡ ግንባታ 94 በመቶ መድረሱን ጠቁመው፤ የግዱቡ የውሃ ማስተንፈሻ ስፒልዌይ ስራም መጠናቀቁን ገልጸዋል። የግድቡ ግንባታ መሉ በሙሉ ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር በርካታ ነዋሪዎችን በመስኖ ልማትና በመጠጥ ውሃ ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ተናግረዋል።
የደባርቅን የመልማት ፀጋ ወደ ተጨባጭ አቅም ለመቀየር ከተማዋን በመሰረተ ልማት ማበልጸግ ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Aug 24, 2026 389
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦የደባርቅን የመልማት ፀጋ ወደ ተጨባጭ አቅም ለመቀየር ከተማዋን በመሰረተ ልማት ማበልጸግ እንደሚገባ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። የደባርቅን ከተማ ለማልማት የተዘጋጀ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር "ደባርቅን እናሳምር ከተማችንን እናድምቅ" በሚል መሪ ሀሳብ በሂልተን ሆቴል እየተካሄደ ይገኛል። በመርሃ ግብሩ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች እና ባለሀብቶች ተገኝተዋል። በገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብሩ "ኑ ተፈጥሮ የገለጠችውን ድንቅ የቱሪስት መስህብ የስሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ መግቢያ በር የሆነችውን ደባርቅ ከተማ በጋራ እናልማ" የሚል ጥሪ ቀርቧል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ደባርቅ የስሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ መግቢያ ከተማ ናት። ይሁን እንጂ ደባርቅ የታሪክ ባለቤትነቷን፣ የቱሪዝም መተላለፊያነቷን የሚመጥን ልማት አልታደለችም ብለዋል። የደባርቅን የመልማት ፀጋ ወደ ተጨባጭ አቅም መለወጥ የሚያስችል እንቅስቃሴ መጀመሩንም ጨምረው ገልጸዋል። በመሆኑም ከተማዋን በማልማት የተፈጥሮ ውበቷን ለመግለጥ ሁሉም በጋራ ትብብር ሊያደርግ ይገባል ብለዋል። የደባርቅ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ከንቲባ ጌትነት ፀጋየ በበኩላቸው፤ ደባርቅ የቀድሞ የሰሜን አውራጃ ከተማ፣ በዓለም ቅርስነት የተመዘገበው የስሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ መገኛ የቱሪዝም ቀዬ መሆኗን ገልጸዋል። ደባርቅ በተፈጥሮ ሀብቶች የበለጸገች የቱሪዝም ማዕከል ብትሆንም የሚገባትን ያህል መልማት ባለመቻሏ የቱሪስቶችን የቆይታ ጊዜ ማራዘም አልቻለችም ነው ያሉት። ስለሆነም መንግሥት ያመጣው የኮሪደር ልማት ተቋዳሽ እንድትሆን ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ ጥሪ አቅርበዋል።  
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች የሕዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጡ ነው
Aug 24, 2026 161
ሳውላ፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በመደመር መንግስት እሳቤ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የህዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጡ መሆናቸውን የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ ገለጹ። አቶ ገብረመስቀል ጫላን ጨምሮ ከክልሉና ከዞኖች የመጡ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች በጎፋ ዞን እና በሳውላ ከተማ በመደመር መንግስት እሳቤ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎችን ተመልክተዋል።   አቶ ገብረመስቀል በወቅቱ እንደገለጹት በክልሉ በመደመር መንግስት እሳቤ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የህዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጡ ነው። በክልሉ ጎፋ ዞንም በግብርናና በኮሪደር ልማት የተከናወኑ ተግባራት የዜጎችን ተጠቃሚነት ያሳደጉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በእንስሳት እና በዶሮ እርባታ ዘርፍ እየተተገበሩ ያሉ ሥራዎች ውጤታማ ናቸው ያሉት አቶ ገብረመስቀል፣ በዘርፉ የተሰማሩ ዜጎችም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በተለይ በሳውላ ከተማ በወተት እና በወተት ተዋጽኦ ምርት ላይ የተሰማሩ ወጣቶች ካፒታላቸውን ከ64 ሺህ ብር መነሻ ወደ 3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ማሳደገቻው ለሌሎች ተሞክሮ ይሆናል ብለዋል። በክልሉ ለሚያጋጥሙ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችም በራስ አቅም ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን አቶ ገብረመስቀል አያይዘው ጠቅስዋል።   በተለይም ካለፈው በጀት ዓመት ጀምሮ ሀብት የማሰባሰብና ሰብል የማምረት ሥራው ተጠናክሮ እየተከናወነ መሆኑን ነው የገለጹት። በጎፋ ዞን ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የልማት ሥራዎች ውጤት ተመዝግቧል ያሉት ደግሞ የጎፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ኢንጂነር ዳግማዊ አየለ ናቸው።   ተደራጅተው በሌማት ትሩፋት መርሀግብር ወደሥራ የገቡ ወጣቶች ከራሳቸው ባለፈ ለሌሎች ወጣቶችም የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻላቸውን ገልጸዋል። በዞኑ በተለይ በዶሮ እርባታ፣ በማር ምርት፣ በወተት ልማትና በሌሎችም ዘርፎች የመጣውን ውጤት ለማስቀጠል ልዩ ትኩረት መሰጠቱንም ጠቁመዋል። ከሦስት ዓመት በፊት በ64 ሺህ ብር መነሻ ካፕታል የአንድ ቀን የዶሮ ጫጩቶችን እርባታ ሥራ እንደጀመሩ የተናገረው ደግሞ ወጣት ሰላሙ ዮናስ ነው።   በሂደት ሥራቸውን ወደ ወተት ላም እርባታ ሥራ እንደቀየሩ ገልጾ በአሁኑ ወቅትም ለሳውላ ከተማ ነዋሪዎች የወተት ምርታቸውን በስፋት እያቀረቡ መሆናቸውን ተናግሯል። የወተት ላሞቻቸው ቁጥር ከ8 በላይመድረሱን የገለጸው ወጣት ሰላሙ፣ ካፒታላቸውም ከ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ መድረሱንና ለአምስት ሰዎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውንም አስረድቷል። ሥራቸውን በማስፋፋት ይበልጥ ውጤታማ ለመሆንም የእንስሳት መኖ ልማት ሥራ እንደጀመሩ ጠቁሞ፣ በመንግስት እየተደረገላቸው ያለ ድጋፍ ለውጤታማነታቸው አጋዥ በመሆኑ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቋል።  
ኢትዮጵያ በሆርቲካልቸር ዘርፍ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብት ምቹ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት አቅም አላት - የሕንድ ባለሀብት ጋጄንድራ ሲንግ
Aug 24, 2026 197
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በአትክልትና ፍራፍሬ የግብርና ልማት ዘርፍ ዓለም አቀፍ የገበያ ተወዳዳሪነትን የሚያጎለብት ምቹ የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት አቅም እንዳላት በግብርና ኢንቨስትመንት የተሰማሩት የሕንድ ባለሀብት ጋጄንድራ ሲንግ ገለጹ። ጋጄንድራ ሲንግ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወላይታ ዞን ቦዲቲ አካባቢ በአቮካዶ ልማት ተሰማርተው እየሰሩ ይገኛሉ። በግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፍም በበርካታ ሀገራት የገበያ ጥናት በማካሄድ ለሆርቲካልቸር ዘርፍ ባላት ምቹ የተፈጥሮ ሁኔታና ጠንካራ የመንግሥት ድጋፍ ምክንያት ኢትዮጵያን መምረጣቸውን ተናግረዋል። በዚህም በኢትዮጵያ የተፈጠረውን ምቹ የግብርና ኢንቨስትመንት ምኅዳር መሰረት ያደረገ የአዋጭነት ጥናት በማካሄድ በፍራፍሬ ልማት ዘርፍ ተሰማርተው እየሰሩ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ በተለይም በሆርቲካልቸር ዘርፍ ያላት ከፍተኛ የመልማት አቅም በመጠቀም ባለሀብቶች መዋዕለ ንዋያቸውን ፈሰስ በማድረግ የሚጠቀሙበት ዕድል የተፈጠረባት ሀገር መሆኗን አንስተዋል። በኢትዮጵያ ካለው የሀገር ውስጥ ገበያ ባለፈ በአትክልትና ፍራፍሬ ዘርፍ በዓለም አቀፍ ገበያ ምርቶችን ማቅረብ የሚያስችል የልማት ከባቢ መፈጠሩንም አስገንዝበዋል። መንግሥት በግብርና ዘርፍ ለተሰማሩ አርሶ አደሮች ድጋፍ እያደረገ ነው ያሉት ጋጄንድራ፤ የኢትዮጵያ መንግሥት ለኢንቨስትመንት የሰጠው ቁርጠኝነትም ምቹ የልማት ምኅዳር ፈጥሯል ብለዋል። በአዲስ አበባ እየተሠራ ያለው ሥራ የከተማዋን ገጽታ ከማሻሻል ባሻገር፤ በቢሾፍቱ እየተገነባ ያለው ግዙፍ የአየር ማረፊያ የመንግሥት የልማት ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን ተናግረዋል። መንግሥት በአቮካዶ ምርት ላይ አበረታች ተግባር እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፤ በገበያ ተደራሽነት ላይም እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ አንስተዋል። ኢትዮጵያ በቡና ወጪ ንግድ ያላትን ልምድ በመጠቀም በሆርቲካልቸር ዘርፍ ግንባር ቀደም ላኪ የመሆን ዕድል እንዳላት አንስተዋል።  
በደብረ ብርሃን ከተማ የሚገነባው የደረቅ ወደብ ተርሚናል የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን ለማሳለጥ ወሳኝ ሚና አለው
Aug 24, 2026 163
ደብረ ብርሃን፤ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል ደብረ ብርሃን ከተማ የሚገነባው የደረቅ ወደብ ተርሚናል በክልሉ በፍጥነት እያደገ የመጣውን የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ለማሳለጥ ወሳኝ ሚና እንዳለው ተገለጸ። በጠቅላላው 275 ሚሊዮን ብር ወጪ በደብረ ብርሀን ከተማ ለሚገነባው የደረቅ ወደብ ተርሚናል ዛሬ የመሰረት ድንጋይ በማስቀመጥ የግንባታ ሥራው በይፋ ተጀምሯል።   በማስጀመሪያ መርሀግብሩ ላይ የአማራ ክልል መንገድ፣ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ቢሮ ሃላፊ ጋሻው አወቀ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ የደረቅ ወደብ ግንባታው በክልሉ በፍጥነት እያደገ የመጣውን የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ሥራዎች ለማሳለጥ ያግዛል። በቢሮው ባለቤትነት ዛሬ የመሰረት ድንጋይ ተቀምጦ የግንባታ ሥራው የተጀመረው የደረቅ ወደብ ሲጠናቀቅ የደብረ ብርሀን ከተማና የማህበረሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ያሳድጋል ብለዋል።   ደብረ ብርሃን ከተማ ከጅቡቲ ወደብ እና ከአዲስ አበባ ከተማ ባላት ቅርበት ምክንያት ምርትን በፍጥነት ከውጪ ወደሀገር ውስጥ ለማስገባትና ለማስወጣት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳላት ገልጸዋል። የወደቡ መገንባትም ተመራጭነቷን ይበልጥ ያሳድገዋል ብለዋል።   እንደ ሃላፊው ገለጻ የደረቅ ወደቡ ግንባታ ሥራ በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ሲጠናቀቅ በቀን ከ1ሺህ በላይ የጭነት ተሽከርካሪዎችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ በድሉ ውብሸት በበኩላቸው እንዳሉት፣ ከከተማው ፈጣን እድገት ጋር ተያይዞ የደረቅ ጭነት ተሽከርካሪዎች ቁጥር ከጊዜ ወደጊዜ እያደገ ነው።   ለዚህም የደረቅ ወደብ ተርሚናሉ መገንባት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ግንባታው በታቀደለት ጊዜ እንዲጠናቀቅ ከተማ አስተዳደሩ አስፈላጊው እገዛና ትብብር ያደርጋል ብለዋል። በተያያዘ ዜና የሰሜን ሸዋ ዞን መንገድ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መምሪያ ከ75 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጭ ያስገነባው የአሽከርካሪና ተሽከርካሪ ብቃት ማረጋገጫ አገልግሎት ማዕከል ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።   በተርሚናል ግንባታ ሥራ ማስጀመሪያ ላይ ከክልሉ፣ ከዞንና ከደብረብርሃን ከተማ አስተዳደር የተውጣጡ የሥራ ሀላፊዎችና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍል ተወካዮች ተገኝተዋል።
በአማራ ክልል በመኸር ወቅቱ ከ3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም እርሻ በዘር ተሸፍኗል
Aug 24, 2026 143
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ)፡- ‎በአማራ ክልል በመኸር እርሻ ከ3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም መልማቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የሰብል ልማት ባለሙያ ወይዘሮ እንዬ አሰፋ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተያዘው የመኸር ወቅት የሰብል ምርታማነትን ማሳደግ የሚያስችሉ የተሻሻሉ አሰራርና ቴክኖሎጂዎች ጥቅም ላይ እንዲውሉ ተደርጓል። ለዚህም ለአርሶ አደሩ በበቂ መጠን ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ ከማቅረብ ባለፈ በየደረጃው በሚገኙ የግብርና ባለሙያዎች የቅርብ ክትትልና ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮው የመኸር ወቅት በኩታ ገጠም እርሻ ለማልማት ከ 3 ሚሊዮን 338 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማረስ ታቅዶ እየተሰራ ሲሆን እስካሁን በተደረገ ጥረት የእቅዱን 96 በመቶ ማሳካት መቻሉን ተናግረዋል። የተሻሻሉ አሰራሮችን በመጠቀም በቆሎ፣ ስንዴ፣ ማሽላ ጤፍና በቆሎን ጨምሮ በ10 ዋና ዋና ሰብሎች በኩታ ገጠም የለሙ ሲሆን ከዚህ ውስጥም 141 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይሰበሰባል ተብሎ ይጠበቃል ብለዋል። በኩታ ገጠም ለለማው ሰብል ከ3 ሚሊዮን 329 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያና 212 ሺህ 381 ኩንታል ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ እንደዋለም ባለሙያዋ አስታውቀዋል።    
በኦሮሚያ ክልል ስራ አጥነትን ለመቀነስና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Aug 24, 2026 189
አዳማ ፤ነሐሴ 18/2018(ኢዜአ )፡-በኦሮሚያ ክልል ስራ አጥነትን ለመቀነስና ምርታማነትን ለማሳደግ፣ በክህሎት ልማት ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን የክልሉ የስራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ አስታወቀ። በኦሮሚያ ክልል ያለውን ከፍተኛ የወጣቶች ቁጥርና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የስራ ፈላጊዎች መጠን ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ዘላቂ የስራ ዕድል መፍጠር የክልሉ መንግስት ዋነኛ ትኩረት ሆኖ ቆይቷል።   ቀደም ሲል የሚደረጉ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎችና የስራ ዕድል ፈጠራ ጥረቶች በቂ የቴክኒክና የክህሎት ክፍተት ባለባቸው ስራ ፈላጊዎች ምክንያት የተፈለገውን ያህል ውጤት ሲያመጡ አልታዩም። በዚህም ምክንያት የክልሉ የስራ ዕድል ፈጠራና ክህሎት ቢሮ ችግሩን ለመፍታት የሙያና ክህሎት ስልጠናዎችን እንደ ዋነኛ መሳሪያ በመጠቀም፣ ከመንግስታዊና መንግስታዊ ካልሆኑ ባለድርሻ አካላት ጋር የተቀናጀ አሰራር በመዘርጋት ላይ ይገኛል። ዛሬ በአዳማ ከተማ እየተካሄደ የሚገኘው የምክክር መድረክም፣ ቢሮው ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት ዜጎችን በሙያና ክህሎት ለማብቃት የሚያደርገው የዚሁ ጥረት አካል ነው።   የቢሮው ሃላፊ ኢንጂነር ኤባ ገርባ በወቅቱ፤ ስራ አጥነትን ከመሰረቱ ለመቀነስ፣ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ተኪ ምርት ለማምረት በሙያ የበቃ የሰው ሃይል በጥራትና በብዛት ማፍራት ወሳኝ ነው ብለዋል። የክልሉ ዜጎች በሙያ ራሳቸውን ችለው ከመደበኛ ስራ በተጨማሪ በክህሎትና ኢንተርፕሩነርሽፕ ራሳቸውን ማጎልበት አለባቸው ብለዋል። ገበያው የሚፈልገውን የሰው ሃይልና የሙያ ልማት ላይ መስራት ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከግብርና፣ ትምህርት ፣ ማዕድን፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂን ጨምሮ ከተለያዩ ሴክተሮች ጋር በጋራ እየሰራን ነው ብለዋል። የቢሮው የክህሎት ልማት ዘርፍ ሃላፊ አቶ ነርሰዲን ቃድ በበኩላቸው የክህሎት ልማቱ መነሻ ገበያ ተኮር ሙያተኞችን ማፍራት ነው ብለዋል።   በየአካባቢው ያሉ ፀጋዎችንና አቅሞችን በመለየት የልማት ፕሮጄክቶች፣ ሆቴሎችና የቱሪዝም መስቦች እንዲሁም የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ ትኩረት አድርገን አጫጭር የሙያ ስልጠና እንሰጣለን ነው ያሉት። በአዲሱ በጀት ዓመት ሰፊ የስራ ዕድል ለመፍጠር የሚያስችሉ ገበያ ተኮር አጫጭር የሙያና ክህሎት ልማት ስልጠናዎች 3 ሚሊዮን ለሚሆኑ ዜጎች በመስጠት ወደ ስራ ለማስገባት መታቀዱን ለአብነት አንስተዋል። ለዚህም በክልሉ 21 ዞኖችና 23 ከተሞች ያሉትን ፀጋዎችና የገበያ ፍላጎቶችን በመለየት የክህሎት ልማት ስልጠና ይሰጣል ብለዋል።   በኦሮሚያ ክልል ትምህርት ቢሮ የሁለተኛ ደረጃ የትምህርት ፕሮግራሞች ዳይሬክተር እጩ ዶክተር መንግስቱ ለታ እንደገለፁት በሙያና ክህሎት የዳበረ የሰው ሃይል ለማፍራት ከስራና ክህሎት ቢሮ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመን አብረን እየሰራን ነው ብለዋል። "በአሁኑ ወቅት ለ7ኛ እና 8ኛ ክፍል ተማሪዎች የክህሎት ትምህርት እየተሰጠ ይገኛል" ያሉት ዳይሬክተሩ ለ11ኛ እና 12ኛ ክፍል ተማሪዎችም የሙያ ትምህርት ለመስጠት 23 የሙያ አይነቶች ተለይተው መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Aug 24, 2026 148
ሚዛን አማን፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ):በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸምና የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በሚዛን አማን ከተማ እያካሔደ ነው።   የቢሮው ኃላፊ አቶ ታሪኩ አካሉ በመድረኩ ላይ እንዳሉት፣ የንግድ ሚዛን ሥርዓትን በማስጠበቅ ጤናማ ግብይት መፍጠር ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ ይገኛል። በዚህም በተጠናቀቀው የ2018 የበጀት ዓመት የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የሚያስችሉ ተግባራት የተከናወኑ ሲሆን ይህም ውጤታማ እንደነበር ተናግረዋል። ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመከላከል በተደረገው የክትትልና የቁጥጥር ሥራ 8 ሺህ በሚሆኑ ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን ገልጸዋል። ሕገ-ወጥ ንግድ የኑሮ ውድነትን የሚያባብስ መሆኑን ጠቅሰው፣ በተግባሩ ላይ በተገኙ ነጋዴዎች ላይ በተወሰደው እርምጃ ከ52 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር በላይ ወደ መንግሥት ካዝና ገቢ ማድረግ እንደተቻለ አቶ ታሪኩ ጠቅሰዋል። በሌላ በኩል የቅዳሜና እሑድ ገበያ ማዕከላትን በማስፋፋት ኑሮን ለማረጋጋት ያለውን አቅም ከግምት ውስጥ በማስገባት ወደ 36 ከፍ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል።   የሚዛን አማን ከተማ አስተዳደር ኢንዱስትሪና ንግድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጌታቸው መለሰ፣ ከተማ አስተዳደሩ ከ2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት በመመደብ የቅዳሜና እሑድ ገበያ ማዕከላትን ማደራጀት መቻሉን ገልጸዋል። የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ በመንግሥት የተነደፉ ኢንሼቲቮችን በአግባቡ መሬት ላይ በማውረድ ሸማቹን ከአላስፈላጊ የዋጋ ጭማሪ መታደግ ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል።   በምዕራብ ኦሞ ዞን የጀሙ ከተማ አስተዳደር ንግድ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ በረከት ደምሴ በበኩላቸው፣ በከተማዋ ያሉ ሁለት የግብይት ማዕከላትን ለማስፋፋት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በማዕከላቱ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት ምርት የማቅረብ ሥራ እየተሠራ ሲሆን፣ የዋጋና ምርት መደበቅ ሕገ-ወጥ ተግባራት ላይ ጠንካራ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም