ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በድሬዳዋ በሸቀጦች ላይ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይደረግ ቁጥጥር እየተደረገ ነው
Apr 10, 2026 197
ድሬደዋ ፤ ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦ በአልን ምክንያት በማድረግ በሸቀጦች ላይ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይደረግ ቁጥጥርና ክትትል እየተደረገ መሆኑን የድሬዳዋ አስተዳደር ገለፀ። ሸማቾች በበኩላቸው ለትንሳኤ በዓል የግብርናና የኢንዱስትሪ ውጤቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እየገዙ መሆናቸውን ተናግረዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ንግድ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አሚኖ ጣሃ ለኢዜአ እንደገለፁት ፤ የነዳጅ እጥረትና በአልን ምክንያት በማድረግ በግብርናና በኢንዱስትሪ ምርቶች ላይ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉ አካላትን በህግ ተጠያቂ ለማድረግ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ወደ ስራ ተገብቷል። ግብረ ሀይሉ ከህብረተሰቡ በሚደርሰው ጥቆማና መረጃዎች መሰረት የኢንዱስትሪ ምርቶች ላይ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በማያደርጉና እጥረት ለመፍጠር የሚፈልጉ አካላትን በህግ ተጠያቂ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት የሚፈልጉ ጥቂት ነጋዴዎች ወቅታዊ ሁኔታን በመጠቀም በህዝቡ ላይ የሚያደርሱትን ጫና ለመከላከል ጠንካራ ክትትል እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን ግብረ ኃይሉ የልኳንዳ ቤቶች የትንሳኤ በአልን ምክንያት በማድረግ በስጋ ዋጋ ላይ ጭማሬ እንዳያደርጉ መግባባት ላይ መደረሱን አቶ አሚኖ ገልጸዋል ። በማህበራትና ዩኒየኖች እንዲሁም በባዛሮችና በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በኩል ለትንሳኤ በአል የፍጆታ ምርቶች በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውንም አስታውቀዋል ። በቅዳሜና እሁድ ገበያ እና ለበዓል በተዘጋጀው የንግድ ባዛር ላይ ምርቶችን ሲሸምቱ የነበሩት ወይዘሮ ትርሲት ጌታቸው እና ወይዘሮ ትቅደም አሰፋ ለበዓል በቂ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች መቅረባቸውን ተናግረዋል። ምርቶቹን በተመጣጣኝ ዋጋ መግዛታቸውን ጠቅሰው አስተዳደሩ እያደረገ የሚገኘውን ቁጥጥርና ክትትል ማጠናከር እንዳለበት ገልጸዋል ። በምርቶች ላይ ያልተገባ የዋጋ ጭማሬ የሚያደርጉ ነጋዴዎች ተጠያቂ እንዲሆኑ የድርሻቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።
በከተሞቹ በትንሳዔ በዓል ገበያ በቂ ምርትና የእርድ እንስሳት ቀርቧል
Apr 10, 2026 225
ሆሳዕና ፤ ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦በሆሳእና፣ ወላይታ ሶዶና ቦንጋ ከተሞች በትንሳዔ በዓል ገበያ በቂ የምርትና የእርድ እንስሳት አቅርቦት መኖሩ ተመለከተ። በሆሳእና ከተማ በትንሳኤ በአል ገበያ የፍጆታ ምርቶችና የእርድ እንስሳት በተመጣጣኝ ዋጋ ግብይት እየተካሄደ መሆኑን ሸማቾችና ነጋዴዎች ገልጸዋል። በከተማው ሄጦ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ አልማዝ ዘውዴ ለበዓሉ የሚሆናቸውን ዶሮ በተመጣጣኝ ዋጋ መግዛታቸውን ተናግረዋል። በገበያው የምርትና የእርድ እንስሳት አቅርቦት በበቂ ሆኔታ መኖሩን የገለጹት ደግሞ በከተማው በሊች አምባ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ተመስገን ታደሰ ናቸው ። ለበዓሉ የሚሆናቸውን ፍየል እንደ አቅማቸው መግዛታቸውን ተናግረዋል። በገበያው የምርት አቅርቦቱ በአማራጭ መቅረብ በመቻሉ ሁሉም አቅሙን ባገናዘበ መልኩ ሸምቶ በዓሉን እንዲያከብር አስቻይ ሁኔታ ስለመፈጠሩም አመልክተዋል። በከተማው በቅመማ ቅመም ንግድ ዘርፍ የተሰማሩት አቶ አክሊሉ ዘውዴ እንደገለፁት፤ ለበዓሉ የሚያስፈልጉ ሽንኩርትን ጨምሮ ሌሎች የቅመማ ቅመም ምርቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ አለመደረጉን ተናግረዋል። ምርቶቹን ከተለያዩ የንግድ ማህበራት በዓሉ ከመድረሱ አስቀድመው ማግኘት በመቻላቸው በተመጣጣኝ ዋጋ እየሸጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዞኑ የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ ሊከሰት የሚችልን ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ ለመከላከል የሚያስችል ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ወደ ተግባር መገባቱን የተናገሩት ደግሞ የሀድያ ዞን ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ተከተል ዶባሞ ናቸው፡፡ ለበዓሉ የሚሆኑ የመሰረታዊና የፍጆታ ምርቶች አቅርቦት ውስንነት እንዳይኖር ከተለያዩ በንግድ ዘርፍ ከተሰማሩ ማህበራት ጋር ትስስር በመፍጠር ምርቱ እንዲቀርብ ስለመደረጉ ተናግረዋል፡፡ እንዲሁም ለበዓሉ የሚሆን የእርድ እንሰሳትም ጭምር በስፋት እንዲቀርብ ተደርጎ ማህበረሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ ሸምቶ በዓሉን እንዲያከብር ተገቢው ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። በተመሳሳይ በወላይታ ሶዶ ከተማ በትንሳኤ በአል ገበያ ምርትና የእርድ እንስሳት በቂ አቅርቦት መኖሩን ነዋሪዎች ገልጸዋል። የከተማው ነዋሪ ወይዘሮ አምሳል አድነው እንደገለጹት፤ በከተማው በግብይት ማዕከላት እና በመደበኛ የገበያ ስፍራዎች የተሻለ አቅርቦት በመኖሩ እንደየአቅማቸው የመገበያየት ዕድል አግኝተዋል። ነጭና ቀይ ሽንኩርት እንዲሁም ዘይትና የዳቦ ዱቄት በተመጣጣኝ ዋጋ መግዛታቸውን ጠቅሰዋል ። አቶ እንድሪያስ ኦይዳ በበኩላቸው፤ ዶሮ እንዲሁም የበግና የፍየል አቅም በሚፈቅደው ልክ ግብይት እየተካሄደ መሆኑን ተናግረዋል ። በከተማው በሰንጋ ገበያ በቂ አቅርቦት መኖሩን ጠቁመው ይሁንና ካለፈው በአል መጠነኛ የዋጋ ጭማሪ መኖሩን አመልክተዋል ። በዞኑ ባሉ ሁሉም አካባቢዎች ከሸማቾች ህብረት ስራ ዩኒየን እና ማህበራት ጋር በመቀናጀት የተለያዩ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በማቅረብ ለህብረተሰቡ ተደራሽ እየተደረገ ነው ያሉት ደግሞ የወላይታ ዞን ንግድና ኢንዱስትሪ ልማት መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ ወይንሸት ሞላ ናቸው። በተመሳሳይ በቦንጋ ከተማም በትንሳኤ በአል ገበያ በቂ የፍጆታ ምርቶችና የእርድ እንስሳት አቅርቦት መኖሩን ሸማቾች ገልጸዋል ። መምህር ማቲዎስ ሳህሌና አቶ መሠረት ተረፈ የዘንድሮ የፋሲካ በዓል ገበያ የተረጋጋ መሆኑን ገልጸው እንደየ አቅማቸው መሸመታቸውን ተናግረዋል። የካፋ ዞን ንግድና ኢንቨስትመንት መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ሀብታሙ ገብረ ስላሴ በበኩላቸው፤ በትንሳኤ በዓል ገበያ የፍጆታ ዕቃዎች እጥረት እንዳይኖር በሸማቾች ሕብረት ስራ ማህበራትና በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በኩል በቂ ምርት መቅረቡን አስታውቀዋል።
በጀጎል ግንብ ውስጥ የሚገነባው የ”ዳር ሀረር” የመልሶ ማልማት ፕሮጀክት ግንባታ ሊጀመር ነው
Apr 10, 2026 110
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦ የሀረሪ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት በጀጎል አለም አቀፍ ቅርስ ውስጥ የሚገነባው የ''ዳር ሀረር'' መልሶ ማልማት ፕሮጀክት ግንባታ በአፋጣኝ ወደ ስራ ማስገባት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ውይይት አድርጓል። ፕሮጀክቱ በአለም ቅርስነት የተመዘገበው የጀጎል አለም አቀፍ ቅርስን ለነዋሪውና ለጎብኚዎች የበለጠ ምቹ ለማድረግ የሚያግዝ ስለመሆኑ ተገልጿል። በውይይቱ ላይም የ''ዳር ሀረር'' የመልሶ ማልማት ፕሮጀክት የሀገር ኩራት ከሆነው የጀጎል አለም አቀፍ ቅርስ ታሪክና ይዘት ጋር በማጣጣምና የጀጎል ባህላዊ የግንባታ ጥበብን በተከተለ መልኩ እንደሚከናወን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ አስታውቋል። የሚገነባው የ''ዳር ሀረር'' የመልሶ ማልማት ፕሮጀክትም በቅርሱ ውስጥ የሚገኙ ነዋሪዎችን ህይወት ለማሻሻል የሚያግዝ መሆኑ ተጠቅሷል። ፕሮጀክቱ የህዝብን ተጠቃሚነት ከማሳደግም ባሻገር የሀረርን ከፍታ ለማረጋገጥ በሚሰሩ ስራዎች የጎላ ፋይዳ እንዳለው ነው የተመላከተው። በፕሮጀክቱም ዘመናዊ አገልግሎት የሚሰጡ ታሪካዊ ይዘታቸውን የጠበቁ የቱሪስት ማረፊያዎች ይገነባሉ ተብሏል። ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅም ሀረርን በምስራቅ አፍሪካ ቀዳሚ የቅርስ ቱሪዝም መዳረሻ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ቢሮው በመረጃው አመልክቷል።
ኢትዮጵያ በዓድዋ ድል ያሳየችውን አህጉራዊ ምሳሌነት ዛሬም በልማት እየደገመችው ነው-አፍሪካውያን
Apr 10, 2026 352
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በዓድዋ ድል ያሳየችውን አህጉራዊ ምሳሌነት ዛሬም በልማት እየደገመችው ነው ሲሉ የዓድዋ ድል መታሰቢያን የጎበኙ አፍሪካውያን ገለጹ። ኢትዮጵያ የጀግንነት ታሪክ መፍለቂያ ሀገር መሆኗን በመጥቀስ፥ የዓድዋ ድል መታሰቢያ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የአፍሪካውያንና የመላው ጥቁር ሕዝቦች አኩሪ የታሪክ ዓምድ መሆኑን ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት የተካሄደው የ16ኛው የአፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም ጉባኤ ተሳታፊዎች የኢትዮጵያና የአፍሪካውያን የጀግንነት የታሪክ ማህደር የሆነውን የዓድዋ ድል መታሰቢያን ጎብኝተዋል። በጉብኝታቸውም የድል ታሪክ ምስክር የሆኑ ቅርሶችንና የጀግንነት አሻራዎችን የተመለከቱ ሲሆን፣ የድል መታሰቢያው ከሀገር ባለፈ ለአፍሪካ የሚተርፍ ትልቅ ትምህርት የያዘ መሆኑን ገልጸዋል። የዓድዋ ድል ድህነትን ለማሸነፍና ለአፍሪካ ብልጽግና በትብብር ለመሥራት ትልቅ መነሳሳትን የሚፈጥር መሆኑንም ተናግረዋል። ከጎብኚዎቹ መካከል ጅቡቲያዊው ኢሳም አብዱልሃኪም በሰጡት አስተያየት፤ ኢትዮጵያ የጀግንነት ታሪክ መፍለቂያ መሆኗን በሙዚየሙ ውስጥ ካየኋቸው ታሪኮች ተረድቻለሁ ብለዋል። የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን ሲተባበሩ ለየትኛውም ፈተና የማይበገሩ መሆናቸውን ያረጋገጠ ደማቅ አሻራ መሆኑንም ተናግረዋል። ይህም ለሁሉም አፍሪካውያን የአይበገሬነትን ትምህርት የሚሰጥ ነው ብለዋል። ከዛምቢያ የመጡት መሲ ችሉ በበኩላቸው፤ የዓድዋ ድል መታሰቢያ የጦርነት ድልን የሚዘክር ብቻ ሳይሆን በዚህ ዘመን ለልማት መትጋትን የሚያስተምርና ወኔ የሚያስታጥቅ እንደሆነ ጠቁመዋል። አፍሪካውያን ከዓድዋ ደማቅ ታሪክ ተምረን ከተባበርን፤ ልክ እንደ ጦርነቱ ሁሉ ድህነትንም ድል ማድረግ እንችላለን ነው ያሉት። በአዲስ አበባ የተመለከቱት ውበትና ዕድገትም ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ያላትን ምሳሌነት በተግባር ማሳየቱን ገልጸዋል። በተመሳሳይ ሱዳናዊው እስማዔል አሊ፤ ዓድዋ ትክክለኛ የአመራር ብቃትና የሕዝብ ቁርጠኝነት የታየበት መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በጥንቱ ጀግንነቷ ብቻ ሳይሆን ዛሬም እያስመዘገበቻቸው በሚገኙ የልማት ስኬቶች ለአፍሪካ አርዓያ ሆና ቀጥላለች ብለዋል።
በዞኑ ነዳጅን በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተጠቃሚዎች በፍትሃዊነት እንዲያገኙ እየተደረገ ነው
Apr 10, 2026 85
ሆሳዕና ፡- ሚያዝያ 2/2018(ኢዜአ)፡- በሀዲያ ዞን የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተግባራዊ በመደረጉ ተጠቃሚዎች ፍትሃዊ አገልግሎት እንዲያገኙ ማስቻሉን የዞኑ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ገለፀ፡፡ የመካከለኛው ምስራቅ ወቅታዊ ሁኔታን ተከትሎ የነዳጅ አቅርቦት ጫናን ለመቋቋም መንግስት ነዳጅን በቁጠባ ለመጠቀም የሚያስችል የመፍትሔ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል፡፡ የመምሪያው ኃላፊ አቶ ተከተል ዶባሞ ለኢዜአ እንደገለጹት ወቅታዊ ችግር የሆነውን የነዳጅ አቅርቦት ችግርን ለመከላከል በመንግሥት የተለያዩ አቅጣጫዎች ተቀምጦ እየተተገበረ ይገኛል፡፡ በነዳጅ አቅርቦት ውስንነት ምክንያት ማህበረሰቡ የሚያገኘው አገልግሎት እንዳይቋረጥ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱን ከህገ ወጥነት ለመከላከልና በቁጠባ ላይ የተመሰረተ ስርጭት ለማከናወን የሚያስችል ግብረ ኃይል ተቋቁሞ ወደ ተግባር ገብቷል ነው ያሉት፡፡ በዞኑ የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱ በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተግባራዊ በመደረጉ ተጠቃሚዎች ፍትሃዊ አገልግሎት እንዲያገኙ አስችሏል ብለዋል፡፡ በሀዲያ ዞን ሌሞ ወረዳ የኖክ 3 የነዳጅ ማደያ አስተባባሪ አቶ መሰረት ምትኩ በበከላቸው ማደያው የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭቱን ለማመጣጠን በመንግሥት በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት አገልግሎት በመስጠት ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡ በማደያው የሚገባውን የነዳጅ ምርት ቅድሚያ የሚሰጠውን በማስቀደም ለታለመለት ዓላማ እንዲውል በተገቢው እየሰሩ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡ አለም አቀፋዊ ችግር የሆነውን የነዳጅ አቅርቦትና ስርጭትን ከብክነት በፀዳ መልኩ መተግበር እንዳለበት የተቀመጠውን አቅጣጫ በመከተል የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት በመወጣት ላይ እንደሚገኙም ነው የገለጹት፡፡ "በሚሰጣቸው የስምሪት ርቀት መሰረት ለነዳጅ መቅጃ የሚሆን ኩፖን እንደሚሰጣቸውና በዚህም ተገቢ የሆነ አገልግሎት እያገኙ " ስለመሆኑ የተናገረው በህዝብ ማመላሻ ትራንስፖርት ማሽከርከር ላይ የተሰማራው ማሙሽ አበበ ነው፡፡ ይህም ለማህበረሰቡ የሚሰጡትን የትራንስፖርት አገልግሎት በተገቢው እንዲያቀላጠፉ ማገዙንም ነው የገለፀው፡፡ በከተማው የትራንስፖርት አገልግሎት ሲሰጡ ያገኘናቸው አቶ ጌታሁን ጸጋዬ እንደገለፁት የነዳጅ አቅርቦት እጥረት ቢኖርም ያለውን በተገቢው እንዲጠቀሙና ማህበረሰቡን እንዲያገለግሉ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡ የሚያገኙትን ነዳጅ በተገቢው ቆጥበው እንዲጠቀሙ የተቀመጠውን ሀገራዊ አቅጣጫ ተግባራዊ ማድረጉ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ስለመሆኑ ጠቁመዋል። ያጋጠመውን ችግር ከግምት በማስገባት ማህበረሰቡን በተገቢው ለማገልገል እንዲቻል እየተደረገ ያለው ጥረት መጠናከር እንዳለበትም ነው የገለጹት፡፡
በአሶሳ ከተማ ለበዓል ገበያ የግብርናና የፍጆታ ምርቶች በበቂ ሁኔታ ቀርበዋል
Apr 10, 2026 222
አሶሳ፤ ሚያዚያ 2/2018 (ኢዜአ)- በአሶሳ ከተማ ለትንሳኤ በዓል ገበያ የሚሆን በቂ የግብርናና የፍጆታ ምርቶች አቅርቦት መኖሩን ሸማቾች እና አቅራቢዎች ተናገሩ። በአሶሳ ከተማ የገበያ ማዕከል ኢዜአ ያነጋገርናቸው ሸማቾች እና አቅራቢዎች እንደተናገሩት የወቅቱ የትራንስፖርት ችግር ፈተና ቢሆንም ለበዓሉ የግብርናና የፍጆታ ምርቶች በበቂ ሁኔታ ይገኛሉ። ለበዓል የሚሆኗቸውን ምርቶች ሲሸምቱ ያገኘናቸው ወይዘሮ ህይወት ሀይሉ እና ወጣት አበበ አዳነ እንደተናገሩት፤ በገበያው በቂ የግብርና ምርቶች ቢኖሩም መጠነኛ የዋጋ ጭማሪ ታይቷል። ይህም የወቅቱን የትራንስፖርት እጥረት ያገናዘበ በመሆኑ ሁሉም እንደሚረዳው የገለጹት ነዋሪዎቹ፣ በገበያው የተጋነነ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር በመንግስት የተሰራው ስራ በተመጣጣኝ ዋጋ ለመሸመት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። በከተማዋ ለበዓሉ የግብርናና የፍጆታ ምርቶች በበቂ ሁኔታ መቅረቡን ጠቁመዋል። በግብርና ምርቶች አቅርቦት ሥራ ላይ የተሰማሩት ሱራፌል በላይ እና መዝገብ አይኑ በበኩላቸው፤ እስካሁን ለበዓል ተብሎ የተለየ የዋጋ ጭማሪ እንዳልተደረገ ተናግረዋል። በቂ የምርት አቅርቦት በመኖሩ ሸማቾች በፈለጉት አማራጭ እየተገበያዩ እንደሆነ ጠቅሰው፣ ምርትን የሚደብቁ እና ያለአግባብ የዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ ይገባል ብለዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አስር ኢብራሂም የትንሣኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ የዋጋ ንረት እና የምርት አቅርቦት እጥረት እንዳይከሰት ከአምራቾች እና ከማህበራት ጋር በመቀናጀት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ቢሮው ያለአግባብ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ አካላት ላይ እየወሰደ ያለውን እርምጃ አጠናክሮ በመቀጠል የተረጋጋ የገበያ ለመፍጠር ከታችኛው መዋቅር ጋር እየሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በክልሉ ለበዓሉ የሚሆኑ በቂ የግብርናና የፍጆታ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረቡ መሆናቸውን አክለዋል።
በጋምቤላ ክልል የነዳጅ ግብይትና ስርጭት መመሪያ ተግባራዊ እየተደረገ ነው
Apr 10, 2026 85
ጋምቤላ፤ ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ) ፦በጋምቤላ ክልል የነዳጅ ግብይትና ስርጭት መመሪያን ተግባራዊ በማድረግ በህዝቡ ላይ ሊደረሱ የሚችሉ ጫናዎችን ለመቀነስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ የነዳጅ ስርጭትና ግብይት መመሪያ ትግበራን ለማሳለጥና ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይትን ለመቆጣጠር በክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር የሚመራ ግብረ ኃይል ተቋቁሞ እየሰራ መሆኑንም ቢሮው ገልጿል። የጋምቤላ ክልል ንግድና እንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኮንግ ኩላንግ ለኢዜአ እንደገለጹት በመካከለኛው ምስራቅ የተከሰተውን አለመረጋጋት ተከትሎ በህዝብ ላይ ሊደርስ የሚችለውን ጫና ለመቀነስ እንደ ሀገር የነዳጅ ግብይትና አቅርቦት መመሪያ ተላልፏል። በክልሉ ለነዳጅ አመላላሽ ቦቴዎች፣ የምግብ ፍጆዎችንና ሸቀጦችን ለሚጭኑና ለህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ለሚሰጡ ተሽከርካሪዎች ቅድሚያ በመስጠት የማስተናገድ ተግባር እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። እንዲሁም በግብርና ልማት ስራ የሚሰማሩ ትራክተሮችና ሌሎች ተሽከርካሪዎች እየተስተናገዱ እንደሚገኙም ተናግረዋል። በክልሉ እየተተገበረ የሚገኘውን ይህንኑ የነዳጅ ስርጭትና ግብይት ለማሳለጥና ህገ-ወጥ የነዳጅ ግብይትን ለመቆጣጠር በክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር የሚመራ ሰባት የፌዴራልና የክልል ተቋማት የተካተቱበት ግብረ-ኃይል ተቋቁሞ እየሰራ መሆኑንም ኃላፊው ገልጸዋል። የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ከሚሰጡ አሽከርካሪዎች መካከል አቶ ጋሻው ተፈራና አብዱልፈታ አህመድ በሰጡት አስተያየት መንግስት ዓለም አቀፋዊ ሁኔታዎችን ታሳቢ በማድረግ ያስተላለፈው የነዳጅ ግብይትና ስርጭት መመሪያ አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። ይሁን እንጂ በማደያዎች ከታሪፍ ጀምሮ የአተገባበር ክፍተቶች መኖራቸውን ጠቁመው በመንግስት የተላለፈ የነዳጅ ስርጭትና ግብይት መመሪያ ሳይሸራረፍ በአግባቡ ስራ ላይ ሊውል ይገባል ብለዋል። የጋምቤላ ከተማ የስፖርት ነዳጅ ማደያ ተወካይ አቶ አዲሱ አሰፋ እንደገለጹት በማደያቸው ከንግድ ቢሮ በሚሰጠው መመሪያ መሰረት ተሽከርካሪዎችን እያስተናገዱ ይገኛሉ። ታሪፉን በተመለከተም መንግስት ባወጣው የዋጋ ተመን መሰረት እየሸጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተሞችን ወደ አምራችነት እያሸጋገረ ነው
Apr 10, 2026 98
ባህር ዳር፤ ሚያዚያ 2/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የተተገበረው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተሞችን ወደ አምራችነት እያሸጋገረ መሆኑን የክልሉ እንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። በተለይም በእንስሳት ሀብት ልማት የተከናወኑ ተግባራት ነዋሪውን ከሸማችነት ወደ አምራችነት ከማሸጋገር ባለፈ ለትንሳኤ በዓል የተሻለ አቅርቦት እንዲኖር እድል ፈጥሯል ብለዋል። ቢሮው የትንሳኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ በእንስሳትና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርት አቅርቦት ዙሪያ ዛሬ መግለጫ ሰጥቷል። የቢሮ ሃላፊው ጋሻው ሙጨ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የሌማት ትሩፋት ከመተግበሩ በፊት ከተሞች ከገጠር የሚመጣው ምርት ተጠቃሚ እንጂ አምራች አልነበሩም። ይህንን ልምድ ለመቀየር በተለይም አካባቢን መሰረት ያደረገ የእንስሳት ልማት ስራ በልዩ ትኩረት ሲከናወን መቆየቱን ገልጸዋል። የከተማ አስተዳደሮች ወጣቶችን በማደራጀት፣ ባለሀብቶችንና ግለሰቦችን በማሳተፍ በእንስሳት ማድለብ፣ በዶሮና በወተት ልማት በማሰማራታቸው ከተሞች አሁን ላይ የራሳቸውን ምርት ማመንጨት ወደሚችሉበት ደረጃ ደርሰዋል ብለዋል። በከተማና በገጠር በተከናወነ የተቀናጀ ስራ ለዘንድሮው የትንሳኤ በዓል ገበያ በተሻለ መልኩ የእርድ እንስሳት፣ የዶሮ፣ የእንቁላልና የወተት ምርቶች በተዘጋጁ ማዕከላት ለህብረተሰቡ እየቀረቡ ይገኛሉ ነው ያሉት። የወተት ምርትም ከክልሉ አልፎ ወደ አዲስ አበባና አጎራባች ክልሎች በስፋት እየቀረበ መሆኑን አስረድተዋል። የከተማ አስተዳደሮች ለወጣቶች ቦታና ብድር በማመቻቸት፣ የእንስሳት ሀብት ልማቱ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ታግዞ የበለጠ ውጤታማ እንዲሆን ትኩረት ተደርጓል ብለዋል።
በጭሮ ከተማ ለትንሳኤ በዓል በቂ የእርድ እንስሳት ቀርቧል
Apr 10, 2026 63
ጭሮ፤ሚያዝያ 2/ 2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሀረርጌ ዞን ጭሮ ከተማ ለዘንድሮው የትንሳኤ በዓል በቂ የእርድ እንስሳት አቅርቦት መኖሩን ሸማቾችና ነጋዴዎች ገለጹ። እንደ ነጋዴዎቹ ገለጻ፤ ለበዓሉ የሚሆኑ የእርድ ሰንጋዎች፣ ፍየሎችና ዶሮዎች በስፋት ለገበያ ቀርበዋል። በእንስሳት ንግድ የተሰማራው ወጣት አሊ መሐመድ እንደገለጸው፤ ለበዓሉ የሚሆኑ የተለያዩ ደረጃ ያላቸው ሰንጋዎች በየዋጋ አማራጫቸው ቀርበዋል። በተለይም የእንስሳት አቅርቦት ምንጭ ከሆነው የገለምሶ አካባቢ በቂ ምርት በመኖሩ፣ ለሸማቹ የሚፈልገውን ያህል ማቅረብ መቻሉን ተናግሯል። ሌላኛው ነጋዴ አቶ ጋዲሳ ደመቀ በበኩላቸው፣ ከተለያዩ አካባቢዎች የተውጣጡ ሰንጋዎችን በተለያየ መጠንና ዋጋ ለገበያ ማቅረባቸውን አረጋግጠዋል። በገበያው ላይ የሚታየውን የዋጋ ሁኔታ በተመለከተ አስተያየታቸውን የሰጡት አቶ ዋሲሁን ጎሳ፣ ከአቅርቦት አንጻር ችግር ባይኖርም መጠነኛ የዋጋ ጭማሪ መታየቱን ጠቁመዋል። እንደ በሬው ሁኔታ ዋጋ ቢለያይም ለበዓሉ የተሻለ አቅርቦት መኖሩን ተናግረዋል። በተመሳሳይ የፍየል ገበያን በተመለከተ አቶ ተከተል ገዙ እንደተናገሩት፣ ባለፉት ቀናት ከነበረው ዋጋ መጠነኛ ጭማሪ ቢታይበትም አቅርቦቱ ግን ጥሩ ነው። በአጠቃላይ በጭሮ ከተማ የትንሳኤ ገበያ ካለፉት ዓመታት በተለየ መልኩ የእንስሳት አቅርቦት የተሻለ መሆኑን ነጋዴዎች እና ሸማቾች ተናግረዋል።
የትውልድ አጀንዳ የሆነውን የባሕር በር ጥያቄ ለማሳካት ወጣቶች በዕውቀትና በንቃት መሳተፍ አለባቸው-የኢትዮጵያ ወጣቶች ፌዴሬሽን
Apr 10, 2026 303
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበርና የትውልድ አጀንዳ የሆነውን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ከግብ ለማድረስ ወጣቶች በዕውቀትና በንቃት መሳተፍ እንዳለባቸው የኢትዮጵያ ወጣቶች ፌዴሬሽን ገለጸ። የኢትዮጵያን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ዘላቂ ለማድረግና እየጨመረ የመጣውን የሕዝብ የልማት ፍላጎት ለማሟላት አስተማማኝ የባሕር በር ማግኘት አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው። ይህንን ብሔራዊ ግብ ለማሳካትም፣መንግሥት ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤት እንድትሆን የሚያስችሉ ውጤታማ የዲፕሎማሲ ሥራዎችን በስፋት እያከናወነ ይገኛል። የኢትዮጵያ ወጣቶች ፌዴሬሽን ዓለም አቀፍ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አምባሳደር አሌክሳንደር ንጉሴ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ የባሕር በር መኖር ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ዕድገት ወሳኝ ነው። አምባሳደር አሌክሳንደር አክለውም መንግሥት የባሕር በርን በሚመለከት ለሚያከናውናቸው ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ስኬታማነት ፌዴሬሽኑ የበኩሉን ሚና ለመወጣት እየሠራ መሆኑን አመልክተዋል። የወጣቶችን ግንዛቤ የሚያጎለብቱ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን ጠቁመው፣የብሔራዊ ጥቅም አጀንዳን በዘላቂነት ለማሳካት ትውልዱ ትልቅ ኃላፊነት እንዳለበት ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበርና የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ከግብ ለማድረስ ወጣቶች በዕውቀትና በንቃት ሊሳተፉ እንደሚገባ ገልጸዋል። በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን የሰጡ ወጣቶች በበኩላቸው፣ የባሕር በር ጥያቄ የትውልዱ አጀንዳ መሆኑን ገልጸዋል። ወጣት አቤኔዘር ኤርሚያስ የባሕር በር ጥያቄያችን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት እያገኘ መሆኑን ጠቅሶ፥ አሁንም ተፅዕኖ ፈጣሪ ወጣቶችን በመጠቀም አጀንዳውን ለዓለም ይበልጥ ማስገንዘብ አለብን ብሏል። ወጣቶች በማህበራዊ ሚዲያ አጫጭር ቪዲዮዎችንና የታሪክ ማጣቀሻዎችን በመጠቀም የኢትዮጵያን የባሕር በር ጥያቄ ተገቢነት ከሕጋዊ፣ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ አውዶች አንጻር ማሳወቅ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሷል። በተመሳሳይ ወጣት ሩት ሸዋንቅጣውና ፌቨን ፍቃዱ የባሕር በር ጉዳይ የመንግሥት ብቻ ሳይሆን የሁሉም ዜጋ ጉዳይ እንደሆነ አንስተዋል። ወጣቱ ሐሳቡን በመግለጽና መንግሥትን በመደገፍ ረገድ ግንባር ቀደም ሚና ሊኖረው እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በሃዋሳ ከተማ የትንሳኤ በዓል ገበያ በቂ የምርት አቅርቦት የታየበትና ዋጋውም የተረጋጋ ነው - ሸማቾችና ሻጮች
Apr 10, 2026 86
ሀዋሳ፤ ሚያዚያ 2/2018 (ኢዜአ)፡-በሃዋሳ ከተማ የትንሳኤ በዓል ገበያ በቂ የምርት አቅርቦት የታየበትና ዋጋውም የተረጋጋ መሆኑን ሸማቾችና ሻጮች ገለጹ። የሃዋሳ ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ በበኩሉ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ጨምሮ በ7 የገበያ ማዕከላት ለበዓሉ የሚሆኑ ምርቶች በስፋት መቅረባቸውን ተናግሯል፡፡ መጪውን የትንሳኤ በዓል ምክንያት በማድረግ በሃዋሳ በተለያዩ የገበያ ማዕከላት ኢዜአ በመዘዋወር የበዓል ግብይትን ተመልክቷል፡፡ በዚህ ወቅት አስተያየታቸውን የሰጡ ሸማቾችና ሻጮች በበዓል ገበያ በቂ የምርት አቅርቦት የታየበትና ዋጋውም የተረጋጋ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አቶ ገመቹ ገሹራ እና ወይዘሮ እርጎ ጫካ የተባሉ የሃዋሳ ከተማ ነዋሪ በከተማ አስተዳደሩ ለበዓሉ የተከፈቱ የገበያ ማዕከላት ከሌሎች ገበያዎች ምርቶችን በቅናሽ ማቅረባቸው ገበያውን እያረጋጋው መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለበዓሉ ሽንኩርት፣ እንቁላል፣ ዱቁትና ሌሎች ለበዓል የሚሆኑ የፍጆታ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ እየተሸጡ መሆኑንና የምርት አቅርቦትም የተሻለ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ መንግስት በዓሉን ምክንያት በማድረግ የዋጋ ጭማሪና የምርት እጥረት እንዳይኖር የተለያዩ የግብይት ማዕከላትን ማደራጀቱ በተለይ የአቅመ ደካሞችና የመንግስት ሠራተኛውን ችግር ይቀርፋል ብለዋል፡፡ ከተማ አስተዳደሩ ገበያን ለማረጋጋት የጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል፡፡ የመላ ሁለገብ ሃላፊነቱ የተወሰነ መሰረታዊ ህብረት ሥራ ማህበር ሰብሳቢ አቶ ኢዮብ አለሙ በበኩላቸው ማህበሩ ለበዓል የሚሆኑ ምርቶችን ለሸማቹ በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ገበያ የማረጋጋት ሥራ እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን ከሌሎች ገበያዎች በተወሰነ ቅናሽ እያቀረቡ መሆኑን ጠቁመው፣ የክልሉ መንግስትና ከተማ አስተዳደሩ ባደረጉላቸው ድጋፍ ከተለያዩ አካባቢዎች ምርቶችን ማስገባታቸውን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ምርቶችን በበቂ ሁኔታ በማቅረብ የተረጋጋ የበዓል ገበያ እንዲኖር ማስቻሉን ገልጸዋል። የሃዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ አገና ኔቶ በበኩላቸው ለትንሳኤ በዓል ገበያ ምርቶችን በበቂ ሁኔታ በማቅረብ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖር ለማድረግ ከተማ አስተዳደሩ ከክልሉና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም በሕብረት ሥራ ማህበራት፣ በቅዳሜና እሁድ ገበያዎች እንዲሁም በአምራቾች አማካኝነት የግብርና፣ የኢንዱስትሪና ሌሎች የፍጆታ ምርቶችን በማቅረብ ሸማቹ በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲሸምት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም የበዓል ገበያ ከማረጋጋት ባለፈ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት የግብይት ሰንሰለቱን ለማሳጠር መሰራቱን ነው የገለጹት። ወቅታዊ ሁኔታው በህብረተሰቡ ላይ ጫና እንዳያሳድር በ7 የግብይት ማዕከላት የተለያዩ የእርድ እንስሳት እንዲሁም በ36 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች አማካይነት ደግሞ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች እየቀረቡ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሰሞኑን ካጋጠመ የነዳጅ እጥረት ጋር ተያይዞ በምርቶች ላይ ያልተገባ ዋጋ የሚጨምሩ ህገ ወጥ ነጋዴዎችን ለመቆጣጠርም ግብረ ሃይል ተቋቁሞ ክትትልና ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ሃላፊው አክለው የተለያዩ የገበያ አማራጮችን በማመቻቸት ገበያውን ለማረጋጋት የተጀመረው ሥራ ውጤታማ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል 14 ነጥብ 86 ቢሊየን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ ፕሮጀክቶች ፈቃድ ወስደዋል
Apr 10, 2026 91
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፡- በበጀት ዓመቱ ያለፉት ወራት14 ነጥብ 86 ቢሊየን ብር ካፒታል ላስመዘገቡ 221 ፕሮጀክቶች የኢንቨስትመንት ፈቃድ መስጠቱን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ አስታወቀ። ፈቃድ የተሰጠባቸው የኢንቨስትመንት ዘርፎችም 90 በግብርና፣ 72 በአገልግሎት እንዲሁም 59 በኢንዱስትሪ መሆኑን የቢሮው ኃላፊ አባስ መሐመድ (ዶ/ር) ለኢዜአ አስረድተዋል። የኢንቨስትመንት ፈቃድ ካወጡት ፕሮጀክቶች መካከል 2 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር ያስመዘገቡት 34 ዳያስፖራ ባለሃብቶች መሆናቸውንም አመላክተዋል። በአጠቃላይ የኢንቨስትመንት ፈቃድ ያወጡት ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ ሲገቡ ለ33 ሺህ 885 ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል እንደሚፈጠሩም ጠቁመዋል። በሌላ በኩል በዘጠኝ ወራት ወደ 9 ቢሊየን 445 ሚሊየን ብር የሚጠጋ ካፒታል ያስመዘገቡ 106 የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች መስፈርቱን አሟልተው የጠየቁት መሬት ተላልፎላቸው ወደ ተግባር እንዲገቡ በክልሉ መንግሥት ውሳኔ መሰጠቱንም አንስተዋል። Ethiopian News Agency #ኢዜአ #ኢንቨስትመንት
ለትንሳኤ በዓል የሚሆኑ የፍጆታ ዕቃዎችና የእርድ እንስሳት በስፋት ቀርበዋል- ነጋዴዎችና ሸማቾች
Apr 10, 2026 86
አምቦ፤ ሚያዝያ 2/2018 (ኢዜአ)፦ በአምቦ ከተማ ለትንሳኤ በዓል የሚሆኑ የፍጆታ ዕቃዎች እና የእርድ እንስሳት በተሻለ ሁኔታ መቅረቡን ነጋዴዎችና ሸማቾች ገለጹ። የከተማው ነዋሪ ወይዘሮ ትግስት ሽፈራው በከተማው ለበዓል ግብይት ተብሎ በተዘጋጀው ስፍራ ላይ ዘይት፣ ዱቄት እና ሌሎች ለበዓል ፍጆታ የሚውሉ ሸቀጦችን ይዘው መቅረባቸውን ገልጸዋል። በተለይም በከተማው ካለው መደበኛ ገበያ አንጻር የዘይትና የዱቄት ዋጋ ተመጣጣኝ መሆኑን ጠቅሰው፣ የበዓል ገበያውም የተረጋጋ ነው ብለዋል። ሌላው እንቁላል ለበዓል ገበያ ያቀረበው ወጣት አበራ አማና በበኩሉ፣ የገበያ ማዕከሉ ለነጋዴውም ሆነ ለሸማቹ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጾ፤ በቂ አቅርቦት በመኖሩ ሸማቹ እንደ ምርጫው እየገዛ መሆኑን ተናግሯል። በከተማው የእርድ እንስሳት ገበያ ውስጥ ያገኘናቸው ሸማች አቶ ገዛኸኝ ሂርጵሳ እንደገለጹት፤ የበግና የፍየል አቅርቦት ከሌላው ጊዜ የተሻለ መሆኑን ገልጸዋል። ሆኖም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር መጠነኛ የዋጋ ጭማሪ መኖሩን ጠቅሰው በቂ አቅርቦት በመኖሩ በአማራጭ ለመገበያየት መቻላቸውን ተናግረዋል። ሌላዋ ሸማች ወይዘሮ ክብነሽ ሙሊሳ፤ የዶሮ አቅርቦት ጥሩ መሆኑን ገልጸው፤ በዓሉን ከቤተሰቦቻቸው ጋር ለማክበር መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። በአምቦ ከተማ አስተዳደር ንግድ ጽሕፈት ቤት የአትክልትና ፍራፍሬ ባለሙያ አቶ ደጀኔ ኢትሳ እንደገለጹት፤ በዓሉን ምክንያት በማድረግ ነጋዴዎች የፍጆታ ዕቃዎችን በበቂ ሁኔታ እንዲያቀርቡ የቅድመ ዝግጅት ሥራ ተከናውኗል። ህብረተሰቡ የኢንዱስትሪና የግብርና ምርቶችን በቀጥታ ከአምራቹ እንዲያገኝ በማድረግ የገበያ መረጋጋት ለመፍጠር ጥረት መደረጉን ገልጸዋል። በከተማው ዙሪያ የሚገኙ አርሶ አደሮችና ማህበራት ያደለቧቸውን እንስሳት ለገበያ እንዲያቀርቡ መደረጉን ጠቅሰው፤ በአሁኑ ወቅት የበሬ ዋጋ እንደ ደረጃው እየተሸጠ መሆኑ ተመልክቷል።
በድሬደዋ ለትንሳኤ በዓል በቂ የእርድ እንሰሳት ለገበያ ቀርበዋል
Apr 10, 2026 89
ድሬደዋ፣ ሚያዝያ 2/2018(ኢዜአ)፡- በድሬደዋ ገበያዎች ለትንሳኤ በዓል በቂ የዕርድ እንሰሳትና ሌሎች የፍጆታ ቁሶች ለገበያ መቅረባቸውን ሸማቾች እና ነጋዴዎች ተናገሩ። የኢዜአ ሪፖርተር በድሬደዋ ቀፊራን ጨምሮ በአሸዋ፣ በሰባተኛ፣ በሳብያንና በታይዋን አካባቢዎች የሚገኙ የገበያ ስፍራዎችን ቃኝቷል። በገበያ ስፍራዎቹ ሲገበያዩ የነበሩ ሸማቾችና ነጋዴዎች እንደተናገሩት፤ ለትንሳኤ በዓል የበሬ፣ የፍየል፣ የዶሮ፣ የቅቤ፣ የቅመማቅመም ምርቶች በበቂ ደረጃ ቀርበዋል። የበሬ ነጋዴው ወጣት መገርሳ ሁሴን እንዳለው በጥሩ መንገድ ያሳደጋቸውን የሐረር ሰንጋዎች ለገበያ አቅርቦ እስከ 200ሺህ ብር በመሸጥ ላይ ይገኛል። ሰንጋዎቹ እንደ ገበያተኛው አቅም የቀረቡ እና መካከለኛዎቹን እስከ 120 ሺህ ብር ፣ አነስተኛዎቹን እስከ 80ሺህ ብር በመሸጥ ላይ መሆኑን ጠቅሶ የዘንድሮ ገበያ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት አንፃር በትላልቅ ሰንጋዎች ላይ ጭማሬ ታይቷል ብሏል። አሸዋ ገበያ በሬ ሲያማርጡና በዋጋ ሲደራደሩ የነበሩት አቶ ግርማ ይመር ፤በተለያዩ የገበያ ቦታዎች በቂ ከብት ለገበያ መቅረቡን ተመልክተው ዘንድሮ በከብት በዋጋ ላይ መጠነኛ ጭማሬ መደረጉን ገልጸዋል። ነገ የበለጠ ምርት ወደ ገበያ ስለሚገባ በተሻለ ዋጋ የተሻለ በሬ እንደሚያገኙ ጠቁመዋል። የፍየል ሙክቶች በብዛት ለገበያ በሚቀርቡበት የአሸዋ ገበያ ለትንሳኤ በዓል በብዛት እና በዓይነት ማግኘት ይቻላል። ፍየል ሲገዙ የነበሩት አቶ ፍሰሐ ዘገየ እንዳሉት፤ በዚህ የገበያ ስፍራ ሁሉም እንደ አቅሙ የፈለገውን ገዝቶ ወደ ቤቱ እየተመለሰ ነው። በፍየሎች ዋጋ ላይ መጠነኛ ጭማሬ ቢስተዋልም እኔም አቅሜ የፈቀደውን መካከለኛ ፍየል ገዝቻለሁ ብለዋል። የፍየል ነጋዴው ናስር አህመድ በበኩላቸው ለትንሳኤ በዓል በቂ አቅርቦት በገበያው በመመቻቸቱ የዘንድሮውን በዓል ልዩ ያደርገዋል ብለዋል። በአሸዋ የፍየል ገበያ ከትልቅ ሙክት፣ እስከ አነስተኛ ፍየል ለገበያ መቅረባቸውን የኢዜአ ሪፖርተር አስተውሏል። በድሬደዋ ትልቁ የቀፊራ ገበያ በብዛት በቀረቡት የዶሮ እና የእንቁላል ምርቶች ላይም መጠነኛ የዋጋ ጭማሪ መታየቱን እና የቅመማቅመም ምርቶች ግን በተለመደው ዋጋ ግብይት እየተካሄደ መሆኑን ወይዘሮ እታለም ታደሰ እና ወይዘሮ ቆንጅት ረታ ገልጸዋል። ቀርሳ ተራ በተባለው የገበያ ስፍራ ዶሮዎችን ያቀረበችው ነጋዴ ወይዘሮ ጀነቲ አህመድ ትልቁን ዶሮ እስከ 1ሺህ 700 ትንሹን ደግሞ እስከ 1ሺህ ብር በመሸጥ ላይ መሆኗን አስታውሳለች።
ለበዓሉ ምርቶች በበቂ መጠንና በተመጣጣኝ ዋጋ ቀርበዋል-ሸማቾች
Apr 10, 2026 85
ጎንደር ፤ሚያዚያ 2/2018(ኢዜአ)፡- ለትንሳኤ በአል የሚያገለግሉ ምርቶች በበቂ መጠንና በተመጣጣኝ ዋጋ በመቅረባቸው አማራጭ ኖሮን ለመገበያየት አስችሎናል ሲሉ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የጎንደር ከተማ ሸማቾች ገለጹ፡፡ በከተማው በ6 ክፍለ ከተሞች በተቋቋሙ የድንኳን ጊዜያዊ ገበያዎች የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች በብዛት፣ በዓይነትና በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ ማቅረብ ተችሏል። የከተማዋ ሸማቾች እንደገለጹት፤ለትንሳኤ በአል የሚያገለግሉ ምርቶች በበቂ መጠንና በተመጣጣኝ ዋጋ በመቅረባቸው አማራጭ ኖሮን ለመገበያየት አስችሎናል። የከተማዋ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ አድና ጠጋው ለኢዜአ እንደገለጹት በመደበኛ ገበያው 70 ብር የሚሸጠውን አንድ ኪሎ ሽንኩርት በጊዜያዊ ገበያው በ45 ብር በመግዛት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። መንግስት በበዓል ወቅት አማራጭ የገበያ እድሎችን ማመቻቸቱ የገቢ መጠናቸው አነስተኛ ለሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደ አቅማቸው በመገበያየት በዓሉን በደስታ እንዲያሳልፉ ያስችላል ብለዋል። ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሪት ክብካብ አለማየሁ በበኩሏ በዓሉን ምክንያት በማድረግ በሸማቾች መሰረታዊ ማህበራት በኩል የቀረቡ የፍጆታ ምርቶች ሸማቹ ማህበረሰብ ተረጋግቶ እንዲሸምት ምቹ የገበያ እድል የፈጠረ ነው ብላለች፡፡ እርሷም ለበዓሉ ዘይት፣ ዱቄትና ስኳርን ከመደበኛ ገበያው ቅናሽ በሆነ ዋጋ መግዛቷን ጠቁማ በጊዜያዊ ገበያው ሌሎች ምርቶችም በተመጣጣኝ ዋጋ መቅረባቸውን ተናግራለች። የዘንድሮ የበዓል ገበያ በቂ የፍጆታ ምርት ወደ ገበያ የገባበትና በዋጋ ደረጃም ቢሆን በተወሰደው የገበያ ማረጋጋት ስራ የሸማቹን ኪስ የማይጎዳ ነው ያለው ደግሞ ወጣት አበበ ዳገት ነው፡፡ የጎንደር ከተማ የራስ ዳሽን ሸማቾች ህብረት ስራ ዩኒየን ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ አድና አለምዬ ዩኒየኑ በ25 ሚሊዮን ብር ወጪ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በማስገባት በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ አቅርቧል ብለዋል። በዚህም ሁሉንም ምርቶች ከሌላው የገበያ ዋጋ እስከ 20 በመቶ በመቀነስ ሁለት ሺ ኩንታል ጤፍ፣ 100 ኩንታል ስኳር፣ የምግብ ዘይትና ፓስታ ለሽያጭ ማቅረቡን አብራርተዋል፡፡
ኢትዮጵያ ከብሔራዊ ልማት አጀንዳ ጋር የተቀናጀ አደጋን የመቋቋም አቅም እየገነባች ነው-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 9, 2026 291
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ ከብሔራዊ ልማት አጀንዳ ጋር የተቀናጀ አደጋን በራስ የመቋቋም አቅም በመገንባት ረገድ ለአፍሪካ የተግባር ምሳሌ መሆኗን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። 16ኛው የአፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም ጉባኤ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀመንበር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲና ሌሎች የጉባኤው ተሳታፊዎች በተገኙበት በአዲስ አበባ ተካሂዷል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በጉባኤው ባደረጉት ንግግር የአየር ንብረት ለውጥ ጉዳት ቢጨምርም ዓለም አቀፋዊ ትብብርና መደጋገፍ እየላላ መጥቷል ብለዋል። በኢኮኖሚ እና የፖለቲካ ለውጦች ለሰብዓዊ ምላሽ የሚውል የድጋፍ ሀብት መቀነሱን አንስተዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አደጋ ጠንቅቃ ከመገንዘብ ባለፈ የጉዳቱ ገፈት ቀማሽ በመሆኗ የመቋቋም አቅምን የሚያጠክሩ እርምጃዎችን መውሰድ መጀመሯን ገልጸዋል። የረጅም ጊዜ ዝቅተኛ የካርቦን ልቀት እና የአየር ንብረት መቋቋም ልማት ስትራቴጂን በመቅረጽ ለሀገራዊ እድገት እና ለዓለም አቀፋዊ ምላሽ ያላትን ቁርጠኝነት ማሳየቷን ጠቅሰዋል። ሀገር በቀል ፖሊሲዎችን በሁሉም መስኮች በውጤታማነት እየተገበረች ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ከብሔራዊ የልማት አጀንዳዎች ጋር የተቀናጀ የአደጋ መቋቋም አቅም እየገነባች ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የምግብ ሉዓላዊነት፣ የኮሪደር ልማት፣ የታዳሽ ኃይል እና የሰብዓዊ ድጋፍ ሉዓላዊነት አደጋን በራስ አቅም የመቋቋምና በፈተና የማትበገር ሀገር የመገንባት ወሳኝ አምዶች መሆናቸውንም አስረድተዋል። ዘላቂ መጻኢ እድልን ለማረጋገጥ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥሩ በማንሳት፥ ከኢትዮጵያ አልፎ ፋይዳና ተሞክሮነታቸው ለአፍሪካ እንደሚተርፍ ገልጸዋል። ከዚህ አኳያ የአፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም አህጉሪቱ በሳይንስና በፈጠራ በመታገዝ በጋራ የመስራትና ችግሮችን የመቋቋም አቅምን የሚያሳይ ነው ብለዋል። ተቋሙ አፍሪካውያን ከአደጋ በኋላ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ ለአደጋ ቀድሞ ወደ መዘጋጀት እንዲሸጋገሩ እያገዘ መሆኑን ጠቅሰው፥ በአጀንዳ 2063 ራሷን የቻለች፣ የማትበገርና የተባበረች አፍሪካን ለመገንባት ትልቅ አቅም መሆኑን ጠቅሰዋል። የመቋቋም አቅምን ለመገንባት በሀገራት፣ በተቋማት እና በዘርፎች መካከል ያለውን ትብብር፣ መተማመን፣ መደጋገፍና የጋራ አመራርን ማጠናከር እንደሚገባ አንስተዋል። ለዚህ ደግሞ አፍሪካ ግዙፍ አቅም፣ ሀብት፣ እውቀት እንዳላት ገልጸው፥ የሚያስፈልገን በአንድነት እና በዓላማ መነሳት ብቻ ነው ብለዋል። ከአደጋ ስጋት ወደ አይበገሬነት የሚደረገው ጉዞ ራዕይን፣ ቁርጠኝነትን እና ቀጣይነት ያለው እርምጃን እንደሚጠይቅም አንስተዋል። የአፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም የአፍሪካ የአንድነትና የሉዓላዊነት ምሰሶ በመሆኑ የያዘው ግብ እንዲሳካ የፖለቲካ ቁርጠኝነት፣ ዘላቂ ፋይናንስ እና ጠንካራ ቴክኒካዊ አቅም እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
የአፍሪካን ችግሮች በአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት ለመፍታት ሀገራት ትብብራቸውን ሊያጠናክሩ ይገባል
Apr 9, 2026 197
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡- የአፍሪካን ችግሮች በአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት በመፍታት ከውጭ ጥገኝነት ለማውጣት ሀገራት ትብብራቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊክ ሀዳዲ ገለጹ። ኢትዮጵያ የምታስተናግደው16ኛው የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አህጉራዊ ጉባኤ "ለሉዓላዊነት መተባበር" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን እየተካሄደ ነው። የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አባል ሀገራትና ታዛቢዎች እንዲሁም የዘርፉ ተዋንያን የሚሳተፉበት ጉባኤው በአፍሪካውያን መካከል ትብብርና አጋርነትን በመፍጠር አህጉራዊ የአደጋ ሥጋትን የመከላከልና የፋይናንስ አቅምን ማጠናከርን ያለመ ነው። ጉባኤው የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም፣ ለአደጋ ስጋት ምላሽ ለመስጠት እና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ አፍሪካ መር መፍትሔ ማፈላለግ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ምክክርና የጋራ መግባባት መፍጠር ያስችላል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊክ ሀዳዲ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የአፍሪካ ሕብረት አባል ሀገራት እንደ አፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም ያሉ ተቋማት ጋር በጋራ መስራት አለባቸው። በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያመጣው ማህበራዊ፣ ኢኮናሚያዊና የስነ-ምህዳር ለውጥ ጊዜ የሚሰጠው አይደለም ብለዋል። አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ያላት ድርሻ ከአራት በመቶ በታች ቢሆንም አምስት በመቶ ጥቅል አህጉራዊ ሀብቷን እያሳጣት መሆኑን ገልጸዋል። አሕጉራዊ ችግሮች አህጉራዊ መፍትሔ እንደሚሹ ገልጸው፤ የአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት ለአፍሪካ ችግሮች ቅድሚያ መስጠት አለባቸው ብለዋል። አሕጉራዊ ማዕቀፎችና ፖሊሲዎች ከዚህ ጋር መጣጣም እንዳለባቸው ጠቅሰው፤ ችግሩን በዘላቂነት በራስ አቅም ለመፍታት በቴክኖሎጂ የታገዘ ቀጣይነት ያለው የፋይናንስ ስርዓት መዘርጋት ይገባል ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በአፍሪካ ሕብረት አባል ሀገራት መካከል ያለው ትብብር በማሳደግ የፋይናንስ አቅም ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። ከተናጠል እርምጃ ይልቅ በአባል ሀገራት መካከል ትብብርን ማጠናከርና ወደ ተግባር መቀየር ይገባል ያሉት ምክትል ሊቀ መንበሯ፤ አህጉራዊ የትኩረት መስኮች ላይ መተባበር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። አፍሪካ ከውጭ በሚመጣ ፋይናንስ ጥገኛ መሆን እንደሌለባት ጠቅሰው፤ ለአፍሪካ መፍትሔ ሀገር በቀል ዕውቀትና ቴክኖሎጂ ቅድሚያ መስጠት ይገባል ብለዋል። ግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት አካታችነት የምርጫ ጉዳይ አይደለም ያሉት ምክትል ሊቀ መንበሯ፤ ሴቶች፣ አካል ጉዳተኞችና ሁሉንም የማህበረሰብ ክፍሎች ማሳተፍ እንደሚገባ ገልጸዋል።
ለትንሳኤ በዓል የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኘን ነው- ሸማቾች
Apr 9, 2026 142
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018(ኢዜአ)፡- በመዲናዋ ለትንሳኤ በዓል የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኙ መሆኑን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ሸማቾች ገለጹ። ኢዜአ ለበዓል ፍጆታ የሚያስፈልጉ ልዩ ልዩ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች አቅርቦት ምን እንደሚመስል የህብረት ስራ ዩኒየኖችና ሸማች ህብረት ስራ ማህበራት የመሸጫ ሱቆች እና መደብሮች ቅኝት አድርጓል፡፡ ቅኝት ባደረገባቸው የሸማች ህብረት ስራ ማህበራትና ዩኒየኖች ለበዓል ፍጆታ የሚያስፈልጉ ምርቶች ማቅረባቸውንና ህብረተሰቡም ሲገበያይ መመልከት ችሏል። የብርሃን ለሸማቾች ህብረት ስራ ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ ይታየው ታደለ ለኢዜአ እንደገለጹት ለትንሳኤ በዓል ተፈላጊ የሆኑ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች ለማቅረብ ቀደም ተብሎ ዝግጅት ሲደረግ ቆይቷል። ከአምራቾች ጋር ትስሰር በመፍጠርና በዩንዮኖች በኩል ያለ ደላላ ጣልቃ ገብነት በቂ ምርት ወደ ህብረት ስራ ማሀበራት ማስገባት መቻሉን አስታውቀዋል፡፡ ይህን ተከትሎ ለትንሳኤ በዓል ዘይት ዱቄት፤ ሽንኩርት ፤እንቁላል እና ሌሎችም ለበዓሉ አስፈላጊ የሆኑ ምርቶችን በስፋት እና በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል፡፡ አውቶቡስ ተራ ሁለገብ ሸማች ሃላፊነቱ የተወሰነ ህብረት ስራ ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ አንዷለም አስማረ በበኩላቸው፤ ለበዓሉ አስፈላጊ የሆኑ የባልትና ውጤቶችን ጨምሮ ሌሎችን ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ እየተከፋፈለ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የብስራት ለጉለሌ ዩኒየን ዋና ስራ አስኪያጅ ሞገስ መንገሻ በዩኒየኑ ባሉት 10 መሰረታዊ ህብረት ስራ ማህበራት በኩል ምርቶቹን ለመሰረታዊ ማህበራትና ለህብረት ስራ ማህበራቱ በጅምላ እየተከፋፈለ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በማህበራቱ ሲሸምቱ ያገኘናቸው ሸማቾች በበኩላቸው፤ ለበዓሉ ተፈላጊ የሆኑ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኙ መሆናቸውን ገልጸዋል። ካነጋርናቸው ሸማቾች መካከል ወይዘሮ ዓለም ለገሰ እንዳሉት ከዘይት ጀምሮ ለበዓል ተፈላጊ የሚባሉ ሽንኩርትና የተለያዩ ግብዓቶች በተመጣጠነ ዋጋ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ ሌላኛዋ ሸማች ወይዘሮ ጤና ይበልጣል በበኩላቸው በሸማቾች በኩል ለበዓሉ የሚያስፈልጉ የተለያዩ ምርቶችን ማግኘታቸውን አንስተዋል፡፡ መንግሥት በህብረት ሥራ ማህበራት አማካኝነት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ የገበያ መረጋጋት ለመፍጠር ያከናወናቸው ተግባራት የሚደነቁ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ወይዘሮ ፍሬህይወት አባይነህ እና ብዙአየሁ አበበ ናቸው፡፡
የምስራቅ ቦረና ዞን የነዳጅና የግብርና ምርቶችን በህገወጥ መንገድ የሚያዘዋውሩ አካላትን የመቆጣጠር ተግባሩን አጠናክሯል
Apr 9, 2026 109
ነገሌ ቦረና፤ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡- የምስራቅ ቦረና ዞን የነዳጅና የግብርና ምርቶችን በህገወጥ መንገድ የሚያዘዋውሩ አካላትን የመቆጣጠር ተግባር ማጠናከሩን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በህገወጥ የነዳጅና የግብርና ምርቶች ዝውውር ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በነገሌ ቦረና ከተማ ተካሄዷል፡፡ በዚሁ ወቅት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱረዛቅ ሁሴን፤ በዞኑ የሚገኙ አንዳንድ ነጋዴዎች በአቋራጭ ለመበልጸግ ምርት በመደበቅ ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ እያደረጉ ይገኛሉ። በተለይም ወቅታዊ ሁኔታውን ምክንያት በማድረግ በህገወጥ መልኩ ነዳጅን የሚያዘዋውሩ አካላት መኖራቸውም ተረጋግጧል ብለዋል። ለዚህም የዞኑ አስተዳደር ግብረ ኃይል አቋቁሞ ከማደያ ውጭ ነዳጅ በሚሸጡ ህገወጦች ላይ ጠንካራ ክትትልና ቁጥጥር እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በተደረገው ጥረትም በርካታ የንግድ ድርጅቶች መታሸጋቸውን፣ የተወሰኑ የንግድ ቤቶች ባለቤቶችም በቁጥጥር ስር ውለው ተጠያቂ መሆናቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም ህብረተሰቡ ያልተገባ የንግድ እንቅስቃሴ እንዲሁም ህገወጥ የምርት እና የሸቀጦች ዝውውር ሲመለከት ለሚመለከተው አካል ጥቆማ እንዲሰጥ ጥሪ አቅርበዋል። በሌላ በኩል በንግዱ ማህበረሰብ ላይ ያልተገባ ድርጊት ሲፈጽሙ የተገኙ የመንግስት ሰራተኞችም ተጠያቂ እየተደረጉ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዞኑ ንግድ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ገልማ ገልገሎ፤ ህገወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመከላከል ከዞን አስተዳደር፣ ከንግድ፣ ከአቃቤ ህግ፣ ከፖሊስና ከሌሎችም ተቋማት የተውጣጣ የክትትልና ቁጥጥር ኮሚቴ ተቋቁሞ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል ብለዋል። ምርት የደበቁ፣ ፍትሀዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ ባደረጉና በኮንትሮባንድ ስራ ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎች ላይ ህጋዊና አስተዳደራዊ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም 177 ሚሊዮን ብር ግምት ያለው የኮንትሮባንድ እቃ ሲያዘዋውሩ የተገኙ 62 ግለሰቦች ፍርድ ቤት መቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ በሀገር ውስጥ ምርቶች ላይ ፍትሀዊ ያልሆነ ዋጋ በሚጨምሩ የንግድ ድርጅቶች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል። የነዳጅ ምርት በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ቅድሚያ ማግኘት የሚገባቸው አካላት እንዲያገኙ ጥብቅ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑንም አስረድተዋል። በውይይት መድረኩ ላይ የተሳተፉት የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪው አቶ ግዛቸው ካሳ፤ በህገወጦች ላይ የተጀመረው ክትትልና ቁጥጥር ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል። ሌላዋ የመድረኩ ተሳታፊ ወይዘሮ አይናለም አየለ በበኩላቸው፤ የዞኑ አስተዳደር ህገወጥነት ላይ የጀመረው ቁጥጥር ውጤታማ እንዲሆን የበኩላቸውን እንደሚወጡም አረጋግጠዋል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በህገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የተገኘ 12 በርሜል ነዳጅ በቁጥጥር ስር ዋለ
Apr 9, 2026 101
ገንዳውኃ፣ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በህገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የተገኘ 12 በርሜል ነዳጅ በቁጥጥር ስር ማዋሉን የወረዳው ፖሊስ አስታወቀ። በመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት ምክንያት የተከሰተውን የነዳጅ አቅርቦት ችግር ለመቋቋም በመንግስት በኩል ግብረ ሃይል ተቋቁሞ የተለያዩ የመፍትሄ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑ ይታወቃል። የነዳጅን አጠቃቀምን በቁጠባ ከማድረግ በተጓዳኝ የነዳጅን ግብይት ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴን መቆጣጠርና ጥብቅ ክትትል ማድረግ እንደሚገባም ተመላክቷል። በዚህም መሰረት በአማራ ክልል በምዕራብ ጎንደር ዞን ቋራ ወረዳ በህገ ወጥ መንገድ ተከማችቶ የተገኘ 12 በርሜል ነዳጅ በቁጥጥር ስር ማዋሉን የወረዳው ፖሊስ አስታውቋል። በወረዳው ፖሊስ ጽህፈት ቤት የወንጀል ምርመራ ክፍል ኃላፊ ኢንስፔክተር ፍቅሩ አባይ፤ በህገ ወጥ መልኩ ተከማችቶ የተገኘው ነዳጅ በገለጉ ከተማ በሁለት ግለሰቦች በመኖሪያ ቤት መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም በህዝብ ጥቆማ በተደረገው ክትትል የነዳጅ ምርቱን ከነተጠርጣሪ ግለሰቦቹ ፖሊስ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ገልጸዋል። ግለሰቦቹ በህገ ወጥ መንገድ ለመክበር በመፈለግ በሀገርና በህዝብ ላይ ጉዳት ለማድረስ የፈጸሙት መሆኑን አንስተው በቀጣይም ጥብቅ ቁጥጥር የማድረግና ተጠርጣሪዎችን በህግ ተጠያቂ የማድረግ ስራ ይቀጥላል ብለዋል።