ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ምርጥ የዘላቂ የደን ልማት አለም አቀፍ እውቅና አገኘ
Oct 15, 2025 118
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 5/2018(ኢዜአ):-የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ምርጥ የዘላቂ የደን ልማት አያያዝና አጠቃቀም በሚል ዘርፍ ከዓለም የምግብና እርሻ ድርጅት (ፋኦ) እውቅና አግኝቷል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ እውቅናውን ያገኘችው በጣሊያን ሮም እየተካሄደ ባለው የዓለም ምግብ ጉባዔ ላይ ነው። የዓለም የምግብ ጉባኤውም የምስረታ በዓሉ አካል ሲሆን፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ በርካታ ሀገራት ተሳትፈዋል። ድርጅቱ ለኢትዮጵያ "በአረንጓዴ አሻራ ዘላቂ የደን ልማት አያያዝና አጠቃቀም" በሚል ዘርፍ ዓለም አቀፍ እውቅና የሰጠ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ መንግስትን ወክለው የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ ሽልማቱን ተቀብለዋል። የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ በመርሃ ግብሩ ባስተላለፉት መልዕክት፥ ፋኦ ርሃብን ለማጥፋት፣ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቀነስና የአካባቢ ጥበቃን ለማጠናከር ላለፉት 80 ዓመታት የላቀ አሻራ ማሳረፉን አንስተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተጀመረው የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ዛሬ በምርጥ የዘላቂ የደን ልማትና ጥበቃ ምሳሌነት እውቅና በማግኘቱ ኮርተናል ብለዋል። በመርሃ ግብሩ በብዙ ቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል የደን ሽፋንን ከ17 ነጥብ 2 በመቶ ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ማሳደጉን ተናግረዋል። ይህ በመሪ ግልፅ ራዕይና በህዝብ ጠንካራ ተሳትፎ የተሳካና ተስፋችንን ያለመለመ ስኬት ነው ያሉት ሚኒስትሯ፥ ይህንን ተጨባጭ ሥራ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው እንዲጎበኙና በዓይን አይተው እንዲመሰክሩም ጋብዘዋል። ድርጅቱ ከኢትዮጵያ ጋር ላለው ለረጅም ጊዜ የጸና አጋርነት ያመሰገኑት ሚኒስትሯ በጋራ ጥረታችን ችግኞችን እየተከልን የተሻለ ነገን ለልጆቻችን መገንባት ጀምረናል ብለዋል። የዓለም የምግብና የእርሻ ድርጅት (ፋኦ) ከዚህ ቀደም በምግብ ዋስትና፣ በተመጣጠነ የምግብ አቅርቦትና በስንዴ ምርት የላቀ አፈጻጸም ላሳዩት ቁርጠኝነት የከበረውን የፋኦ አግሪኮላ ሜዳሊያ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መሸለሙ ይታወሳል። በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የዓለም የምግብና የእርሻ ድርጅት (ፋኦ) 80ኛ የምስረታ ዓመት የድርጅቱን ያለፉት ዓመታት ስራዎች በሚዳስሱ እንዲሁም ቀጣይ ራዕዩን በሚገልጡ ዝግጅቶች እያከበረ ይገኛል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ለልማት ሥራዎች መፋጠን ተሳትፏችንን እናጠናክራለን - ባለሀብቶች
Oct 15, 2025 83
ጋምቤላ፤ ጥቅምት 5/ 2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል ለተጀመሩ የልማት ሥራዎች መፋጠን ተሳትፏቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በተለያዩ የንግድና የኢንቨስትመንት ዘርፎች የተሰማሩ ባለሃብቶች ገለጹ። በክልሉ የልማትና የንግድ እንቅስቃሴ ዙሪያ በጋምቤላ ከተማ የተዘጋጀ የውይይት መድረክ ተጠናቋል ። ከውይይት መድረኩ ተሳታፊዎች መካከል በግብርና ኢንቨስትመንት የተሰማሩት ባለሃብት አቶ ኡሞድ ኡገር እንደገለጹት በክልሉ ለተጀመሩ የኮሪደርና ሌሎች ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ የልማት ሥራዎች መሳካት የበኩላቸውን ተሳትፎ ለማድረግ ዝግጁ ናቸው። የአቅመ ደካማ ቤቶችን መገንባትን ጨምሮ በሌሎች የልማት ስራዎች ሲሳተፉ መቆየታቸውን የገለጹት ደግሞ በግብርና ኢንቨስትመንት የተሰማሩት አቶ ንጉስ በራ ናቸው። በቀጣይም በክልሉ በተጀመሩ የኮሪደርና ሌሎች ስራዎች ተሳትፏቸውን ይበልጥ አጠናከረው ለመቀጠል ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሌላዋ በሆቴል ስራ የተሰማሩት ወይዘሮ አምሳለ ገብረወልድ በሰጡት አስተያየት የንግዱ ማህበረሰብ በክልሉ የሰላምና የልማት ስራዎች ተሳትፏችንን እናጠናክራለን ብለዋል ። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ በመድረኩ ማጠቃለያ ላይ እንዳሉት ለክልሉ ልማትና እድገት መፋጠን የባለሀብቱ ተሳትፎ ወሳኝ ነው ። የንግዱ ማህበረሰብና ባለሀብቱ በልማት ስራዎች ተሳትፏቸውን ሊያጠናክሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል ።
የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ ሪፎርም እና የልማት ስራ ድጋፍ ማድረጉን ይቀጥላል-የባንኩ ፕሬዝዳንት አጃይ ባንጋ
Oct 15, 2025 157
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፦ የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ ሪፎርም እና የልማት ስራ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የባንኩ ፕሬዝዳንት አጃይ ባንጋ አስታወቁ። የዓለም ባንክ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) አመታዊ ስብሰባ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ነው። በገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ የተመራው ከፍተኛ የልዑካን ቡድን በዓመታዊው ስብሰባ ላይ እየተሳተፈ ይገኛል። ልዑካን ቡድኑ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ ገዥ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ከፍተኛ አማካሪ ተክለወልድ አጥናፉ እና ሌሎች ከፍተኛ ባለስልጣናት ያካተተ ነው። የመንግስት ከፍተኛ ልዑካን ቡድኑ ከዓለም ባንክ ፕሬዝዳንት አጃይ ባንጋ ጋር ተወያይቷል። የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ የዓለም ባንክ ለኢትዮጵያ ልማት ያደረገውን የረጅም ጊዜ እና ዘርፈ ብዙ ድጋፍ አድንቀዋል። ባንኩ ለኢትዮጵያ ቁልፍ የኢኮኖሚ ዘርፎች ያለው አጠቃላይ የፋይናንስ ማዕቀፍ ከ16 ቢሊዮን ዶላር በላይ መሻገሩን አመልክተዋል። ሚኒስትሩ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙን አስመልክቶ ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን ጠንካራ የኢኮኖሚ እድገት፣የወጪ ንግድ እና ሬሚታንስ እድገት፣ የውጭ ምንዛሬ ክምችት ማደግ እና የዋጋ ንረት መቀነስ በሪፎርሙ ከተገኙ ውጤቶች መካከል እንደሚጠቀሱ አንስተዋል። በውይይቱ አቶ አሕመድ፥ የኢትዮጵያ መንግስት ቁልፍ የልማት የትኩረት መስኮችን አንስተዋል። የግብርና ትራንስፎርሜሽን ማፋጠን፣ የሰው ሀብት ልማት ኢንቨስትመንት ማሳደግ፣ የግል የፋይናንስ ሀብት ማሰባሰብ፣ አማራጭ የፋይናንስ መፍትሄዎች መፈለግ እንዲሁም ቀጣናዊ እንዲሁም የባለብዙ ወገን ትብብርን ማጠናከር ሚኒስትሩ ያነሷቸው የትኩረት አጀንዳዎች ናቸው። የዓለም ባንክ ፕሬዝዳንት አጃይ ባንጋ፥ ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መሪነት እያደረገቻቸው ያሉ ጠንካራ እና ታሪካዊ የኢኮኖሚ ሪፎርሞችን አድንቀዋል። ፕሬዝዳንቱ የኢትዮጵያን ሀገራዊ ምክክር ያደነቁ ሲሆን ሂደቱ ማህበራዊ ትስስርን በማጠናከር ኢትዮጵያ አቅሟን ተጠቅማ ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ እድገት እንድታስመዘግብ የሚያስችል ቁልፍ እርምጃ እንደሆነ ተናግረዋል። የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ የልማት ጉዞ፣ የሪፎርም አጀንዳ እና የልማት የትኩረት መስኮችን ለመደገፍ ቁርጠኛ ነው ብለዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ሂደቱ ዘላቂ የሆነ የልማት ውጤት እንዲያመጣ ድጋፉን እንደሚያደርግ መግለጻቸውን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል።
የመሰረተ ልማት ስራዎች ተጠብቀው የዜጎች ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ህግ የማስከበር ስራችንን እናጠናክራለን - ፌዴራል ፖሊስ አመራሮችና አባላት
Oct 15, 2025 142
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፡-በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተከናወኑ ያሉ የመሰረተ ልማት ስራዎች ተጠብቀው የዜጎች ተጠቃሚነትን የበለጠ ለማረጋገጥ ህግ የማስከበር ተግባራቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አመራሮችና አባላት ገለጹ። የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ አመራሮችና አባላት ከእንጦጦ ፓርክ እስከ አቃቂ ቃሊቲ ድረስ የተሰሩ የኮሪደር ልማት እና ልዩ ልዩ መሰረተ ልማቶች ስራዎችን ዛሬ ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ወቅት ኢዜአ ያነጋገራቸው የፌዴራል ፖሊስ አመራሮችና አባላት እንደገለጹት፤ በከተማዋ በተገነቡ መሰረተ ልማት ስራዎች እጅግ ተደንቀዋል። በፌዴራል ፖሊስ የወንጀል መከላከል ጤና አገልግሎት ሃላፊ ዋና ኢንስፔክተር አብደላ አደላ፤ አዲስ አበባን ጨምሮ በመላው አገሪቷ እየተሰሩ የሚገኙ የልማት ስራዎች የሰላም ፍሬ ማሳያዎች መሆናቸውን ተናግረዋል። የአገር ልማት የሚረጋገጠው ሰላም በአስተማማኝ ሁኔታ ሲሰፍን ብቻ መሆኑን ጠቁመው፤ "ሰላምና ልማት የማይነጣጠሉ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው" ብለዋል፡፡ የፌዴራል ፖሊስ ሰላምን የማስጠበቅና ልማትን እንዲፋጠን የማድረግ ተግባርን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው የተናገሩት፡፡ በፌዴራል ፖሊስ ሆስፒታል የግዥ ሃላፊ ኮማንደር ባዬ ሽፈራው በበኩላቸው እንደገለጹት፤ የከተማዋ ውበት፣ መሰረተ ልማቶች አገሪቷ ፈጣን እድገት ውስጥ መሆኗን አመላካቾች ናቸው። ፖሊስ የልማት አደናቃፊ እና የፀረ ሰላም ሃይሎችን እኩይ ተግባር እያከሸፈ መምጣቱን አውስተው፤ ይህን ተግባሩን ወደፊትም አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡ በፌዴራል ፖሊስ የልዩ ፀረ ሽብር ኮማንዶ አባል ዋና ኢንስፔክተር አየለ አሸናፊ፤ በዛሬው ጉብኝታችን አገራችን እየተጓዘችበት ያለውን ከፍታ በተግባር ያየነበትና ያረጋገጥንበት ነው ብለዋል፡፡ የፌዴራል ፖሊስ ረዳት ኢንስፔክተር ማርታ ወረቁ በበኩላቸው፤ የህዝብንና የአገርን ሰላም ለማረጋገጥ የሚከፈለው ዋጋ ለዚህ ዓይነት የልማት ስራዎች አብቅቶናል ብለዋል። በፌዴራል ፖሊስ የወንጀል መከላከል ተቋም ጥበቃ መምሪያ የሬጅመንት አዛዥ ኮሎኔል ማቲዮስ ሸጋው እንደገለጹት፤ ፖሊስ ህዝብና መንግስት በሚያከናውናቸው የልማት ስራዎች የራሱን አሻራ የማኖር ተግባሩን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡
አልማ "የብቁ ወጣት ፕሮግራም" የተሰኘ ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ፕሮግራም ይፋ አደረገ
Oct 15, 2025 65
ባሕርዳር፤ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ) ፡-የአማራ ልማት ማህበር (አልማ) በቀጣዮቹ ሶስት ዓመታት ከ67 ሺህ በላይ ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ "የብቁ ወጣት ፕሮግራም" የተሰኘ ፕሮግራም በይፋ ጀመረ። የፕሮግራሙን ማስጀመሪያ በተመለከተ በተዘጋጀው አውደ ጥናት የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የማህበሩ አመራሮችና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በባሕርዳር ከተማ ተካሂዷል። የአልማ ስራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢና በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ ድጋፍ የሚሹ ወጣቶችና አካል ጉዳተኞችን የሙያ ክህሎታቸው አድጎ እራሳቸውን እንዲችሉ ማብቃት ያስፈልጋል። ለዚህም ይፋ የተደረገው ፕሮግራም የበኩሉን አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አንስተዋል። በፕሮግራሙ ተጠቃሚ ከሚሆኑት ወጣቶች መካከል 80 በመቶ ሴቶች፣ 10 በመቶ አካል ጉዳተኞች ቀሪዎቹ ደግሞ ሌሎች መሆናቸውን ተናግረዋል። ወጣቶቹ የስራ ዕድል ፈጠራና የቴክኖሎጂ ተጠቃሚ እንዲሆኑ በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸው፤ ለፕሮግራሙ ውጤታማነት ሁላችንም ተቀናጅተን ልንረባረብ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። የአማራ ልማት ማህበር (አልማ) ዋና ስራ አስፈፃሚ መላኩ ፈንታ፤ በወቅቱ በሰጡት ማብራሪያ ማህበሩ በክልሉ የዜጎችን የልማት ተጠቃሚነት መሰረት አድርጎ እየሰራ መሆኑን አንስተዋል። በዛሬው እለትም ይፋ የተደረገው "ብቁ ወጣት ፕሮግራም" የተሰኘው ፕሮግራም በተለይም ወጣቶችን በተለያዩ የልማት ስራዎችና አገልግሎቶች በማሳተፍ ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣዮቹ ሶስት ዓመታት የሚተገበረው ፕሮግራም ከአጋር አካላቶች ጋር በመተባበር ከ67 ሺህ በላይ ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን አንስተዋል። በክልሉ 23 ወረዳዎች ለመተግበር እቅድ የተያዘው "የብቁ ወጣት" ፕሮግራም በተያዘው ዓመት 23 ሺህ ወጣቶችን የስራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ በቅንጅት የሚሰራ መሆኑ ታውቋል። በአውደ ጥናቱ ላይ ሙሉነሽ ደሴ (ዶ/ር)ን ጨምሮ ሌሎችም የክልሉ የስራ ሃላፊዎችና የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
ከደመወዝ ማሻሻያ ጋር ተያይዞ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በሚያደረጉ ነጋዴዎች ላይ የሚወሰደው ህጋዊ እርምጃ ይጠናከራል
Oct 15, 2025 73
ገንዳውሃ፣ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ):-ለመንግሥት ሰራተኛው ከተደረገው የደመወዝ ማሻሻያ ጋር ተያይዞ በዞኑ ያልተገባ ዋጋ በሚጨምሩ ነጋዴዎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የምዕራብ ጎንደር ዞን ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ አስታወቀ። መምሪያው በገንዳውሃ ከተማ በወቅታዊ ንግድና ግብይት ሥርዓት ዙሪያ ከንግዱ ማሕበረሰብ እና ሌሎች አጋር አካላት ጋር ውይይት አካሄዷል። በውይይት መድረኩ ላይ የዞኑ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ ጌትነት በሊሁን እንዳመለከቱት፤ ሕገወጥ ንግድን በመከላከል የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር በትኩረት እየተሰራ ነው። በመሆኑም ጤናማ የንግድ አሰራር እንዲሰፍን እና ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴ እንዳይኖር የተጠናከረ የቁጥጥር ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፤ ሁሉም ማሕበረሰብ ይህንን በመደገፍ የድርሻውን እንዲወጣ አንስተዋል። የንግዱ ማሕበረሰብ ሕጋዊ የንግድ ሥርዓትን በመከተል ሸማቹን በቅንነት ማገልገል እንዳለበት አሳስበዋል። በተለይም ለመንግሥት ሰራተኛው ከተደረገው የደመወዝ ማሻሻያ ጋር ተያይዞ ያልተገባ ዋጋ በሚጨምሩ ነጋዴዎች ላይ ፈቃዳቸውን ሙሉ በሙሉ መሰረዝን ጨምሮ የሚወሰደው ሕጋዊ እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል። በዞኑ የሚመረቱትን የቅባት እሕሎች በሕጋዊ የግብይት ሰንሰለት እንዲያልፉና በኮንትሮባንድ እንዳይወጡ ጥብቅ ቁጥጥር እንደሚደረግም ተናግረዋል። የገንዳውሃ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አብዱልከሪም ሙሃመድ በበኩላቸው፤ የከተማዋ ሕገወጥ ንግድ የሰላም ፀር መሆኑን ሁሉም በመገንዘብ በሕግና ስርዓት መስራት እንዳለበት አስገንዝበዋል። በከተማዋ የንግድ ስራን ቀልጣፋ፣ ሸማቹንና ነጋዴውን እኩል ተጠቃሚ እንዲሆኑ አስተዳደሩ የሚጠበቅበትን እንደሚወጣም ገልጸዋል። ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል አቶ ጅብሪል ሙሀመድ በሰጡት አስተያየት፤ ያልተገባ ጥቅም ለማግኘት የሚጥሩ ነጋዴዎችን ለማጋለጥ ዝግጁ መሆናቸውንም ተናግረዋል። ሕገወጥነትን መከላከል የጋራ ስራ ነው ያሉት ደግሞ ሌላኛው ተሳታፊ አቶ ጓዴ አስማረ ሲሆኑ፤ መንግስት ተገቢውን እርምጃ በመውሰድ ማስተማር እንዳለበት አስተያየት ሰጥተዋል። በውይይት መድረኩ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ኀላፊዎች፣ ነጋዴዎችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳተፈዋል።
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹ የማድረግ ሥራ ውጤት እያስገኘ ነው
Oct 15, 2025 99
ይርጋጨፌ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹና ጽዱ የማድረግ ሥራ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሥራና ክህሎት ቢሮ ሃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) ገለጹ። በክልሉ ጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ከተማ በ70 ሚሊዮን ብር ወጪ በህብረተሰቡ ተሳትፎ በሁለተኛ ምዕራፍ የተከናወኑ የኮሪደርና የተለያዩ የልማት ሥራዎች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሥራና ክህሎት ቢሮ ሃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት በክልሉ ከተሞችን ለነዋሪዎች ምቹና ውብ የማድረግ ሥራ ውጤት እያስገኘ ነው። በተለይ የኮሪደር ልማት እና የመሰረተ ልማት ማስፋፊያ ሥራዎች የከተሞችን ውበትና ጽዳት በማሳደግ ለኑሮ የሚመች አካባቢን ከመፍጠር ባለፈ ጤነኛ ዜጋን ለማፍራት እያገዘ ነው ብለዋል። በክልሉ ህብረተሰቡን በማሳተፍ በ64 ከተሞች የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆነን አንስተው፤ ይህም የውስጥ አቅምን ወደ ልማት ለመለወጥ ማስቻሉን ተናግረዋል። ከተሞችን በፕላን በመምራትና የገቢ አቅማቸውን በማሳደግ የተጀመሩ ልማቶችን ማጠናከር እንደሚገባም አሳስበዋል። በዞኑ ባሉ ከተሞች መሠረተ ልማትን ለማስፋፋትና አገልግሎትን ለማዘመን በተሰራው ሥራ የህብረተሰቡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች እየተመለሱ መምጣታቸውን ያነሱት ደግሞ የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ናቸው። ከተሞችን በውስጥ አቅም ተወዳዳሪ ማድረግ እንደሚቻል ከይርጋጨፌ ከተማ ትምህርት መውሰድ እንደሚቻል ገልጸው፤ በቀጣይ የከተማዋን ተሞክሮ ወደሌሎች ለማስፋት ይሰራል ብለዋል። በተለይ የከተማዋን ልማት ለማጠናከር የዞኑ አስተዳደር ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል። የይርጋጨፌ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ታደለ ጥላሁን በበኩላቸው የውስጥ አቅምን በማጠናከር በከተማው ልማትን የማረጋገጥ ሥራ እየተሰራ ነው ብለዋል። በዛሬው እለትም በህብረተሰቡ ተሳትፎ በ70 ሚሊዮን ብር ወጭ በሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት የተከናወኑ ሥራዎች፣ ሁለት ድልድዮችና አረንጓዴ ስፋራዎችን ጨምሮ ሰባት የመሠረተ ልማት ማስፋፊያዎች ለምረቃ በቅተዋል ብለዋል። በከተማው መሠረተ ልማትን ከማስፋፋት ባለፈ አገልግሎትን በማዘመን የህብረተሰብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ መቻሉንም ከንቲባው ገልጸዋል። በዛሬው እለትም የማዘጋጃ ቤታዊ እንዲሁም የገቢና ንግድ አገልግሎቶች ዲጂታል መደረጋቸውን አንስተው፤ በቀጣይ ሁሉንም የከተማ አገልግሎቶች ከወረቀት አሰራር ነጻ የማድረግ ሥራ ይሰራል ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደሩ የመንግስት የሥራ ሃላፊዎች፣ የተለያዩ የህብርተሰብ ክፍል ተወካዮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
የንጋት ሐይቅ የዓሳ ምርት ለብዙዎቻችን የስራ እድል የፈጠረና ተጠቃሚም ያደረገ ነው- ወጣቶች
Oct 15, 2025 130
አሶሳ፤ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፦የንጋት ሐይቅ የዓሳ ምርት ለብዙዎቻችን የስራ እድል የፈጠረና ተጠቃሚም ያደረገ መሆኑን በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ዓሳ በማስገር ስራ ላይ የተሰማሩ ወጣቶች ተናገሩ። በታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ላይ የተንጣለለው ንጋት ሐይቅ ከ70 በላይ ደሴቶች ያሉት ትልቅ የቱሪስት መስህብ ስፍራ ሲሆን በዓሳ ምርቱም ለአካባቢው ነዋሪዎች የገቢ ምንጭ እየሆነ ነው። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በርካታ ወጣቶች በሐይቁ ላይ ዓሳ በማስገርና ለገበያ በማቅረብ ከራሳቸው አልፈው ሌሎችም ተጠቃሚ እንዲሆኑ እያደረጉ ይገኛሉ። በዚሁ ስራ ላይ ተሰማርተው ከሚገኙት መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው ወጣቶች የንጋት ሐይቅ የዓሳ ምርት ለብዙዎቻችን የስራ እድል የፈጠረና ተጠቃሚም ያደረገን ነው ብለዋል። በክልሉ መንጌ ወረዳ ፍርዶስ ቀበሌ በማህበር ተደራጅተው ዓሳ ከሚያሰግሩት ወጣቶች መካከል ሚካኤል አነጁም እና ረመዳን ሰኢድ፤ የንጋት ሐይቅ አስደናቂ የመዝናኛ ስፍራ እና የዓሳ ምርት መገኛ በመሆን ለብዙዎቻችን ጠቅሞናል በዚህም ተደስተናል ሲሉ ተናግረዋል። የሐይቁ የዓሳ ምርት በአካባቢው አዲስ የገቢ ምንጭ እና ሁነኛ የምግብ አማራጭ ሆኖ እየተሰራበት መሆኑንም ወጣቶቹ ገልጸዋል። በክልሉ ተጠልለው የሚገኙ የሱዳን ስደተኞችም ከወጣቶቹ የዓሳ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ በመረከብ የምግብ ቤት በመክፈት እየሰሩ መሆኑን ተናግረው፥ በዚህም ደስተኞች ነን ብለዋል። ከስደተኞቹ መካከል አብዱልባጊ ኑር እና ወጣት እንድሪስ አረያ፤ የህዳሴ ግድብ ከብርሃን ምንጭነቱም ባለፈ በተለይም በዓሳ ምርት ከኢትዮጵያዊያን አልፎ ለእኛም ጠቅሞናል ብለዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ስደተኞችን በመቀበል የክፉ ቀን ወዳጅ በመሆን ላሳየው መልካምነት በማመስገን የአካባቢው ማህበረሰብም በሁሉም ነገር በጋራ እንድንጠቀም እያደረገን በመሆኑ ኢትዮጵያ ሁለተኛ ቤታችን ሆናለች ሲሉ ተናግረዋል። በክልሉ የመንጌ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ሳላህ ራህመተላ፤ የህዳሴው ግድብ በረከቶች ብዙ መሆናቸውን አንስተው፥ በተለይም የንጋት ሐይቅ ዓሳ ደግሞ የወጣቶችን ህይወት እየቀየረ መሆኑን ገልጸዋል። በወረዳው በርካታ ነዋሪዎችና በአካባቢው ተጠልለው የሚገኙ የሱዳን ስደተኞችም የዓሳ ሃብቱ ተጠቃሚዎች መሆናቸውን አንስተዋል። የንጋት ሐይቅ 74 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውኃ የተንጣለለበት፤ከ70 በላይ ደሴቶች ያሉት እና 187 ሺህ 400 ሔክታር ስፋት ያለው መሆኑ ይታወቃል።
ክልሎች የልማት ዕቅዶችን ወጥ በሆነ መልኩ በመፈጸም የሀገራዊ እድገትን ሊያፈጥኑ ይገባል
Oct 15, 2025 123
አሶሳ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፦ ክልሎች የልማት ዕቅዶችን ወጥ በሆነ መልኩ በመፈጸም ሀገራዊ እድገትን ሊያፋጥኑ እንደሚገባ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) ተናገሩ። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ከተማ ከክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በልማት ዕቅዶች አተገባበር ዙሪያ የምክክር መድረክ አካሂደዋል። በመድረኩ ላይ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ የልማት ዕቅዶችን በመፈጸም ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት አየተመዘገበ ነው። ለዚህም ክልሎች ያላቸውን ሀብት በተገቢው ለማልማት የሚያስችል የልማት ዕቅዶችን ከራሳቸው ነባራዊ ሁኔታ ጋር በማጣጣም መስራታቸው የራሱ ድርሻ ነበረው ብለዋል። ይህንን ለማቀላጠፍና የክልሎቹን የልማት ዕቅዶች የመፈጸም እቅም ወጥ ለማድረግ ሚኒስቴሩ ዲጂታል መተግበሪያዎችን ሥራ ላይ እያዋለ መሆኑን ጠቅሰዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻደሊ ሀሰን በበኩላቸው፤ የክልሉን አቅም ያገናዘበ የልማት ዕቅድ በመተግበር ሀገራዊ ዕድገቱን ለማፋጠን እየተሰራ ነው ብለዋል። ክልሉ ከማዕድን በተጨማሪ ለእርሻ እና ለተለያዩ ኢንቨስትመንት ሥራዎች ምቹ መሆኑን ጠቅሰው ይህን በማልማት የህዝብን ተጠቃሚነት ለማሳደግ አቅም እንደሚሆን ጠቁመዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ያዘጋጀው ዲጂታል ቴክኖሎጂም የልማት ዕቅዶችን በዘመናዊ መንገድ በመከታተል ስራውን ለመምራትና ትክክለኛ ሪፖርት ለማግኘት እንደሚያስችል ገልፀዋል። በመድረኩ ላይ የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በከር ሻሌ (ዶ/ር) እንዲሁም የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ
Oct 15, 2025 57
በጋምቤላ ፤ጥቅምት5/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል የአካባቢ ስነ-ምህዳርን በመጠበቅና በመንከባከብ የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ገለፀ። ቢሮው ለአርሶ አደሮች የገጠር የመሬት የይዞታ ማረጋገጫ ደብተርና ካርታ የመስጠት መርሃ ግብር ዛሬ በጋምቤላ ከተማ አስጀምሯል። የቢሮው ኃላፊ አቶ ፓል ቱት በወቅቱ እንዳሉት በክልሉ የአካባቢ ስነ-ምህዳርን በመጠበቅና በመንከባከብ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው ። በተለይም በክልሉ ፈጣንና ዘላቂነት ያለው የግብርና እድገት እንዲመዘገብ አርሶ አደሩን በግብርና ግብዓቶች ከመደገፍ ባለፈ የገጠር መሬት ባለቤትነታቸውን የማረጋገጥ ስራዎች በመከናወን ላይ መሆኑን ተናግረዋል። የገጠር መሬት የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር መስጠት ያስፈለገው አርሶ አደሩ ያለውን የእርሻ መሬት ስነ-ምህዳር በባቤትነት ስሜት እንዲጠብቅና በዘላቂነት አልምቶ እንዲጠቀም ለማስቻል ነው ብለዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ በ10 ወረዳዎች ከ11 ሺህ ለሚበልጡ አርሶ አደሮች የገጠር መሬት የይዞታ ማረጋገጫ ደብተርና ካርታ ተዘጋጅቶ እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ተወካይ አቶ ኡኬሎ ኡማን በወቅቱ እንዳሉት መንግስት የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሻሻል የሚያስችሉ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። ከዚህም ውስጥ ለአርሶ አደሩ የገጠር መሬት የባለቤትነት የይዞታ ማረጋገጫ ደብተርና ካርታ መስጠት መሆኑን ጠቅሰው ይህም መሬቱን በአግባቡ መዝግቦ ለመያዝና ለማስተዳደር ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል። በዕለቱ የገጠር መሬት የይዞታ ማረጋገጫ ደብተርና ካርታ ከወሰዱ አርሶ አደሮች መካከል አቶ ኡዶል ኡቶንግ መንግስት ለይዞታቸው ደብተርና ካርታ መስጠቱ የእርሻ መሬታቸውን በዘላቂነት አልመተው ለመጠቀም እንደሚያስችላችው ተናግረዋል። ሌላዋ አርሶ አደር አቦያ ኡኩሪ በበኩላቸው የይዞታ ማረጋገጫ ደብተርና ካርታው መሬታቸውን በአግብቡ አልምተው እንዲጠቀሙ ዋስትና እንደሚሆናቸው ገልጸዋል። ቢሮው ባለፉት ዓመታት በዘላቂ የመሬት አያያዝ ፕሮጀክት ከ95 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን የገጠር መሬት የይዞታ ማረጋገጫ ደብተርና ካርታ መስጠቱ ታውቋል።
በደሴ ከተማ የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ይበልጥ የሚያጠናክሩ የልማት ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Oct 15, 2025 70
ደሴ ፤ ጥቅምት 5/2018(ኢዜአ)፡-በደሴ ከተማ አስተዳደር የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ይበልጥ ማጠናከር የሚያስችሉ የልማት ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የከተማው አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሳሙኤል ሞላልኝ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ የ2018 ሩብ የበጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በደሴ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ ላይ የከተማው አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሳሙኤል ሞላልኝ እንደገለጹት፣ የደሴ ከተማን ለጎብኚዎቿ፣ ነዋሪዎችና ባለሃብቶች ይበልጥ ምቹና ሳቢ ለማድረግ ሲሰራ ቆይቷል። በተያዘው የበጀት ዓመትም ከአንድ ነጥብ ሶስት ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ተመድቦ የሕብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚነት ማጠናከር የሚያስችሉ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ቀደም ብለው የተጀመሩ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅና አዳዲሶቹን ማፋጠን ላይ በማተኮር እንደሆነ አስረድተዋል። ተጨማሪ የኮሪደር ልማት፣ ከመናፈሻ መገንጠያ- ወሎ ዩኒቨርሲቲ እንዲሁም አረብ ገንዳ የአስፋልት መንገድና ሌሎች ፕሮጀክቶችን ለማከናወን የሚያስችል እንቅስቃሴ ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። የሥራ እድል ፈጠራ፣ የገቢ አሰባሰብ፣ ገበያ ማረጋጋት፣ የመሶብ አንድ ማዕከል፣ የተማሪዎች ምገባና የመልካም አስተዳደር ስራዎችም ሌሎቹ ትኩረት የተደረገባቸው መሆኑን ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው ተናግረዋል። የደሴ ከተማ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ ዮናስ እንዳለ በበኩላቸው፤ ባለፉት ሶስት ወራት ገበያውን ለማረጋጋት የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት አስመዝግበዋል ብለዋል። የተለያዩ የገበያ ማዕከላትን በማቋቋም ሸማቹን ማህበረሰብ ከአምራቹ ጋር በቀጥታ በማገናኘት የፍጆታ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ መደረጉን አስረድተዋል። በትምህርት፣ በጤናና በሌሎችም ማህበራዊ ዘርፎች ተስፋ ሰጭ ውጤት መመዝገቡን የተናገሩት ደግሞ የከተማው አስተዳደር የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ተወካይና የሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ መምሪያ ኃላፊ ምሳዬ ከድር ናቸው። የትምህርት ቤት ማስፋፋፊያና የጤና ተቋማት ግንባታን በማከናወን የየዘርፉን ውጤታማነት ለማስቀጠል እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በመድረኩ የከተማና የክፍለ ከተማ አመራሮችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።
የደመወዝ ጭማሪው የኑሮ ውድነት ጫናን የሚቀንስና የሥራ ተነሳሽነትን የሚፈጥር ነው -የመንግስት ሠራተኞች
Oct 15, 2025 67
አርባ ምንጭ ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ):- መንግስት ያደረገው የደመወዝ ጭማሪ የኑሮ ውድነት ጫናን የሚቀንስና የሥራ ተነሳሽነትን የሚፈጥር መሆኑን በአርባ ምንጭ ከተማ የተለያዩ ተቋማት የመንግስት ሠራተኞች ተናገሩ። በመንግስት ይፋ የተደረገውን የደመወዝ ጭማሪ ተከትሎ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አርባ ምንጭ ከተማ የተለያዩ ተቋማት ሰራተኞችን የኢዜአ ሪፖርተር ተዘዋውሮ አነጋግሯል። በአስተያየታቸውም የመንግስት የደመወዝ ጭማሪ የኑሮ ውድነት ጫናን የሚቀንስና የሥራ ተነሳሽነትን የሚፈጥር ስለመሆኑ አንስተው ህዝብን በላቀ ብቃትና ቁርጠኝነት ለማገልገል ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል። የክልሉ የንግድ ቢሮ ሰራተኛ አቶ ካሣሁን ለማ፤ የደመወዝ ጭማሪው የኑሮ ውድነት ጫናን ትርጉም ባለው መልኩ የሚያቃልልና የስራ ተነሳሽነትን በማሳደግ ውጤታማ አገልግሎት ለመስጠት ያግዛል ብለዋል። መንግስት የደመወዝ ጭማሪውን ተከትሎ የገበያ ንረት ለመፍጠር የሚሞክሩ ህገወጥ ነጋዴዎች ላይ የተጠናከረ ቁጥጥር እያደረገ መሆኑን አንስተዋል። የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ሠራተኛ የሆኑት ወይዘሮ ሰብለ ቢያድግልኝ፤ መንግስት ያደረገው የደመወዝ ጭማሪ ተገቢ እና ወቅታዊ ምላሽ የተሰጠበት መሆኑን ገልጸዋል። የመንግስት ሠራተኞች የመግዛት አቅምን የሚጨምር ኢኮኖሚያዊ ጫናዎችን የሚቀንስ በመሆኑ መደሰታቸውን ገልጸው መንግስት ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በሚያደርጉ ህገ ወጦች ላይ የተጠናከረ እርምጃ መውሰድ አለበት ብለዋል። በአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ፋይናንስ ፅህፈት ቤት የሚሰሩት አቶ ስንታየሁ ሀብታሙ፤ በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሁለት ጊዜ የደመወዝ ጭማሪ መደረጉ መንግስት የዜጎቹን ችግሮች የመፍታት ቁርጠኝነቱንና የኑሮ ውድነት ጫናን የማቃለል ጥረቱን ያሳየበት መሆኑንም ተናግረዋል። በመሆኑም የመንግስት የደመወዝ ጭማሪ የኑሮ ውድነት ጫናን የሚቀንስና የሥራ ተነሳሽነትን የሚፈጥር በመሆኑ ሁላችንም ተደስተናል ብለዋል።
በምዕራብ ኦሮሚያ አካባቢዎች ግንባታቸው የተቋረጠ የመንገድ ፕሮጀክቶችን በፍጥነት ለማጠናቀቅ እየተሰራ ነው
Oct 15, 2025 63
ጊምቢ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ):-በምዕራብ ኦሮሚያ አካባቢዎች ግንባታቸው የተቋረጠና የተጓተቱ የመንገድ ፕሮጀክቶችን በፍጥነት በማጠናቀቅ የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄ ለመመለስ እየሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መልካ በቀለ ገለጹ። የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ከምዕራብ ኦሮሚያ አካባቢዎች የስራ ሀላፊዎች ጋር በአካባቢው የመንገድ ፕሮጀክቶች አፈፃፀም ላይ ያተኮረ ምክክር አድርጓል። የአስተዳደሩ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መልካ በቀለ በወቅቱ እንዳሉት በምዕራብ ኦሮሚያ አካባቢዎች በተለያዩ ምክንያት ግንባታቸው የተቋረጡና የግንባታ አፈጻጸማቸው ዝቅተኛ የሆኑ መንገዶችን በፍጥነት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት እንዲበቁ በትኩረት ይሰራል። አሁን ላይ ግንባታቸውን በአጭር ጊዜ ለማጠናቀቅ ሥራ ከሚጀመርባቸው አራት መንገዶች መካከል ሁለቱ ግንባታቸው የተጓተተ ሲሆን ቀሪዎቹ ደግሞ በተለያዩ ምክንያቶች ግንባታቸው ተቋርጦ የነበሩ መሆኑን አስረድተዋል። የመንገድ ፕሮጀክቶቹን ግንባታ ለማስቀጠል መንግስት 6 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በጀት መያዙን ተናግረው የመንገዶቹን ግንባታ በፍጥነት ለማጠናቀቅም ከዞኑ አስተዳደርና ከህብረተሰቡ ጋር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል። የመንገዶቹ ግንባታ ሲጠናቀቅ ከዚህ በፊት የነበረውን የትራንስፖርት እንቅስቃሴ ችግር ከመፍታት ባለፈ ለህብረተሰቡ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር አመልክተዋል። በብልጽግና ፓርቲ የምዕራብ ወለጋ ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ በዳሳ ዳባ፣ በዞኑ በነበረው የጸጥታ ችግርና በተለያዩ ምክንያቶች ግንባታቸው የተቋረጡ መንገዶችን መልሶ ለማስጀመር በሚደረገው ጥረት የዞኑ አስተዳደር አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል፡፡ በየደረጃው ያሉ የዞኑ አመራሮችም ለመንገዱ ግንባታ መፋጠን የድርሻቸውን እንዲወጡም አሳስበዋል፡፡ በመድረኩ የተሳተፉ የወረዳ አመራሮች በበኩላቸው አሁን ላይ ግንባታቸው ተጀምሮ የተቋረጡና የተጓተቱ መንገዶችን ለማጠናቅቅ በሚደረገው ጥረትም ህብረተሰቡን የማስተባበር ሀላፊነታቸውን በአግባቡ እንደሚወጡም ገልጸዋል፡፡
በሀዲያ ዞን በመኸር እርሻ ከለማው ሰብል ከ8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዷል
Oct 15, 2025 89
ሆሳዕና፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፡-በሀዲያ ዞን በመኸር እርሻ ከለማው ሰብል ከ8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ግብ ተጥሎ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ ሀብታሙ ታደሰ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት በዞኑ በ2017/18 የመኸር ወቅት እርሻ ከ156 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለምቷል። ከዚህ ውስጥ ከ51 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት በክላስተር መልማቱን ገልጸው፣ ይህም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የጎላ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል። በዞኑ በመኸር እርሻ ከለማው መሬት ከ8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ግብ ተጥሎ እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። ዕቅዱን ለማሳካት በምርት ዘመኑ የግብርና ግብአት አቅርቦት እጥረት እንዳይከሰት መሰራቱን የገለጹት ሃላፊው፣ ምርጥ ዘርን ጨምሮ የግብአት አቅርቦቱ የአርሶ አደሩን ፍላጎት መሰረት በማድረግ ተሰራጭቷል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የሰብል እንክብካቤ ሥራው በተቀናጀና በልዩ ትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ነው ያስታወቁት። የሰብል እንክብካቤና ጥበቃ ሥራው አርሶ አደሩን በማሳተፍ እየተከናወነ መሆኑን የገለጹት የመምሪያ ኃላፊው፣ ለዚህም የፀረ አረም መድሃኒት ከማቅረብ ባለፈ በግብርና ባለሙያ ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ ምስራቅ ባዳዋቾ ወረዳ አምቡርሴ አንጁሎ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ግርማ ሶደኖ በበኩላቸው በቀበሌው 51 አባወራዎችና እማወራዎች በክላስተር ተደራጅተው በ57 ሄክታር መሬት ላይ ጤፍ እያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የጤፍ ማሳቸውን በማረምና ጸረ ተባይ መድሀኒት በመርጨት እየተንከባከቡ እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡ እንደ አርሶ አደሩ ገለጻ ማሳቸውን በክላስተር ማልማት ከጀመሩ ወዲህ ከግብአት አቅርቦት በተጨማሪ በግብርና ባለሙያዎች ተገቢ ድጋፍና እገዛ እያገኙ ነው። በእርሻ ሥራ ለሰብል የሚደረግ እንክብካቤ ምርታማነትን ለማሳደግ ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ደግሞ ሌላኛው የወረዳው አርሶ አደር ጥጋቡ ሎዴቦ ናቸው። በመኸር ወቅት ካለሙት ጤፍና ሌሎች ሰብሎች የተሻለ ምርት ለማግኘት በአሁኑ ወቅት የሰብል እንክብካቤ ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የእንክብካቤ ሥራውን የቤተሰብ አባላትን ጭምር በማሳተፍ እያከናወኑ መሆናቸውን የገለጹት አርሶ አደር ጥጋቡ፣ በግብርና ባለሙያዎች የሚሰጣቸውን ምክር በአግባቡ ተግባራዊ በማድረግ ላይ መሆናቸውንም ገልጸዋል። አሁን ካለው የሰብሉ ቁመና የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ ጠቁመው ለዚህም የሰብል እንክብካቤ ሥራቸውን እንደሚያጠናክሩ ተናግረዋል፡፡
በክልሉ ለተጀመሩ የልማት ኢንሼቲቮች ስኬታማነት የባለሃብቶች ሁለንተናዊ ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል-ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ
Oct 15, 2025 48
ጋምቤላ ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ):- በክልሉ ለተጀመሩ የልማት ኢንሼቲቮች ስኬታማነት የባለሃብቶች ሁለንተናዊ ተሳትፎ ይበልጥ ሊጠናከር እንደሚገባ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። በክልሉ ከሚገኙ ባለሃብቶችና የንግድ ማህበረሰብ አባላት ጋር በመንግስት የልማት ኢንሼቲቮችና የንግድ እንቅስቃሴዎች ዙሪያ በጋምቤላ ከተማ የውይይት መድረክ እየተካሄደ ነው። የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት በክልሉ ያለውን ሰላም በማጽናት እንደ ሀገር የታለመውን የማንሰራራት ዘመን እውን ለማድረግ ባለሃብቶች ተሳትፏቸውን ይበልጥ ሊያጠናክሩ ይገባል። በክልሉ እንደ ሀገር የተጀመረውን የኮሪደር ልማትን ጨምሮ የተለያዩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በመሆኑም በክልሉ እየተከናወኑ ለሚገኙ የልማት ስራዎች ስኬታማነት ሁሉም ባለድርሻ አካል የበኩሉን አስተዋፅኦ ሊያበረክት እንደሚገባ አሳስበዋል። በተለይም በክልሉ በተለያዩ የንግድና የኢንቨስትመንት ስራዎች የተሰማሩ ባለሃብቶች እየተካሄዱ የሚገኙ የልማት ስራዎችን በመደገፍ ረገድ ተሳትፏቸውን እና ትብብራቸውን ይበልጥ አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ገልጸዋል። የምክክር መድረኩ ዋና ዓላማም የክልሉ ባለሃብቶችና የንግዱ ማህበረሰብ አባላት የልማት እንቅስቃሴዎች ዙሪያ ውይይት በማድረግ የአጋርነት ሚናቸውን እንዲያጠናክሩ ለማስቻል መሆኑን ርዕሰ መስተዳድሯ ተናግረዋል። በውይይት መድረኩ ላይም የተለያዩ የመነሻ ጽሁፎች ቀርበው በባለሃብቶችና በንግዱ ማህበረሰብ አባላት ውይይት እየተደረገባቸው ነው።
በንጋት ሐይቅ ላይ 70 የሚደርሱ የወጣት ኢንተርፕራይዞች በዓሳ ማስገር ተደራጅተው ወደ ሥራ ገብተዋል
Oct 15, 2025 97
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ):- በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የንጋት ሰው ሰራሽ ሐይቅ ላይ 70 የሚደርሱ የወጣት ኢንተርፕራይዞች በዓሳ ማስገር ተደራጅተው እየሰሩ እንደሚገኙ የግብርና ሚኒስቴር አስታውቋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ - የንጋት ሐይቅ የረቂቅ ማስተር ፕላን ጥናት ማስጀመሪያ የምክክር መድረክ በቢሾፍቱ ከተማ ተካሂዷል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት÷ ሕዳሴ ግድብ የፈጠረው የንጋት ሐይቅ ለበርካታ ዜጎች በረከት መሆን ጀምሯል ብለዋል። የንጋት ሐይቅ አሁን ላይ በዓመት ከ15 ሺህ ቶን በላይ ዓሳ ማምረት የሚያስችል አቅም እንዳለው ጠቅሰው በ2017 ዓ.ም በጀት ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ 5 ሺህ ቶን የዓሳ ምርት ለገበያ መቅረቡን ገልጸዋል። የሐይቁን ከፍተኛ የዓሳ ምርታማነት አቅም ለማሳደግ የንጋት የተቀናጀ ማስተር ፕላን ዝግጅት የአሰራር ሥርዓት ለመዘርጋት እየተሰሩ የሚገኙ ስራዎችን እንደሚያግዝ ተናግረዋል። በንጋት ሐይቅ ላይ ለዓሳ ማስገር ስራ አስፈላጊ መሳሪያዎች የተሟሉላቸው 70 የሚደርሱ የወጣት ኢንተርፕራይዞች ስራ መጀመራቸውን አስታውቀዋል። የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጌታሁን አብዲሳ በበኩላቸው÷ ለንጋት ሐይቅ የተቀናጀ ማስተር ፕላን ዝግጅትና ትግበራ አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል። የንጋት ሐይቅ የ240 ኪሎ ሜትር የውሃ አካልና ከሰባ በላይ ደሴቶች ለትራንስፖርት፣ ለዓሳ ምርታማነትና ለሆቴልና ቱሪዝም ልማት ምቹ መሆኑን በመጥቀስ ለበርካታ ወጣቶች መልካም ዕድል ይዞ መምጣቱን ገልጸዋል። በሕዳሴ ግድብ የተፈጠረው የንጋት ሐይቅ ላይ በዓሳ ማምረት የስራ ዕድል የተፈጠረላቸው በርካታ ወጣቶች ሃብትና ጥሪት እያፈሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ከውሃና ኢንርጂ፣ ከግብርና ሚኒስቴርና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር የተጀመረው የንጋት ሐይቅ የተቀናጀ አስተዳደር ማስተር ፕላንም ስኬቶችን ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል፡፡ በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የተቀናጀ የውሃ ሃብት አስተዳደር መሪ ሥራ አስፈፃሚ ደበበ ደፈርሶ÷ ማስተር ፕላኑ የንጋት ሐይቅ የፈጠራቸውን ጸጋዎች በሥርዓት ለማስተዳደር ታልሞ እየተዘጋጀ መሆኑን ገልጸዋል። የንጋት ሐይቅ የዜጎችን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የዓሳ ሃብት፣ የትራንስፖርትና ተያያዥ ትሩፋቶች ይዞ መምጣቱን ገልጸዋል። ማስተር ፕላኑም ቀጣይ የሚፈጠሩ ከተሞችን ታሳቢ በማድረግ የንጋት ሐይቅ የውሃ ሃብትና ከባቢውን በመጠበቅ የተፋሰሱን ሀገራት የውሃ ሃብት ዘላቂነት የሚያስጠብቅ መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን የከተማ ፕላንና ዲዛይን ክፍል ኃላፊ ይኸነው ኃይሉ÷ የማስተር ፕላን ዝግጅቱ የንጋት ሐይቅ የቱሪዝም፣ ከተማ ልማት፣ የትራንስፖርት አገልግሎት መሠረተ ልማትን ለማዘመን ጉልህ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተናግረዋል።
በጉራጌ ዞን የመስህብ ሥፍራዎችን በማልማትና በማስተዋወቅ የተጀመሩ ተግባራት ውጤት እያመጡ ነው
Oct 15, 2025 179
ወልቂጤ ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ):- በጉራጌ ዞን የቱሪዝም መስህብ ሥፍራዎችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ የተጀመሩ ተግባራት ውጤት እያመጡ መሆኑን የዞኑ ባሕልና የቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ ። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ መሠረት አመርጋ፤ ዞኑ ካላው እምቅ የቱሪዝም አቅምና መዳረሻዎች አንፃር ይገኝ የነበረው ጥቅም አነስተኛ ሆኖ መቆየቱን አስታውሰዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ይህን መቀየር የሚያስችል ሥራ በተቀናጀና ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በዞኑ ያሉ የተፈጥሮ፣ ሰው ሰራሽና እና ታሪካዊ የመሥህብ ሥፍራዎችን በማልማትና በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል ። በተለይም በዞኑ ያሉ የቱሪዝም መሥህቦችን ለማስተዋወቅ እና ለማስጎብኘት ከግሉ ዘርፍ፣ ከመገናኛ ብዙኃንና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት መሰራቱ ውጤት እያመጣ መሆኑን ተናግረዋል። በዘንድሮው የመስቀል በዓል ከሃገር ውስጥ እና ከተለያዩ ዓለም ሃገራት በርካታ ጎብኚዎች ወደ ዞኑ መምጣታቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም 230 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን አንስተዋል ። ከውጭ የሚመጡ ጎብኚዎች የ"ጀፎረ" የገጠር ኮሪደር ልማት ላይ የብስክሌት ሽርሽር ማድረግ እየተለመደ መምጣቱ እና በየአካባቢውም የሕዝቡ እንግዳ ተቀባይነት የቱሪስቱን የቆይታ ጊዜ ለማራዘም እያስቻለ እንደሆነም ጠቅሰዋል። በዚህም የእደ ጥበብ ወጤቶች ተፈላጊነት መጨመር እና ለአገልግሎት ሰጪ ተቋማት መነቃቃት መፍጠሩን አውስተው፤ ለቱሪስቶች ማረፊያ የሚሆኑ የሆቴሎችና ሌሎች አመቺ ሥፍራዎችን የማስፋፋት ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል። ዞኑ በዘርፉ ካለው አቅም አንጻር ብዙ ሊሰራ እንደሚገባ ያነሱት ሃላፊዋ፤ ለዚህም ይረዳ ዘንድ አዳዲስ የመሥህብ ሥፍራዎችን የማልማትና የማስተዋወቅ እንዲሁም መሰረት ልማት የማሟላት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል ።
የባህር በር ጥያቄው ከፍትሃዊ ተጠቃሚነት እሳቤ የመነጨና የህልውና ጉዳይ ነው- ምሁራን
Oct 15, 2025 137
ሮቤ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ):- የባህር በር ጥያቄው ኢትዮጵያ ከምትከተለው የፍትሃዊ ተጠቃሚነት እሳቤ የመነጨና የህልውና ጉዳይ በመሆኑ በሁሉም ዘንድ ሊደገፍ ይገባል ሲሉ የመደወላቡ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ። የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የውሃ ኃብት አጠቃቀምና የሃይድሮሎጂ ረዳት ፕሮፌሰር አለማየሁ አባተ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት የጀመረችው ጥረት በቀጣናውና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተሰሚነቷን በተሻለ መልኩ የሚያሳድግ ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴ ነው። ኢትዮጵያ የግዙፍ ኢኮኖሚና ከፍተኛ የሕዝብ ቁጥር ባለቤት እንዲሁም ለቀይ ባህር በቅርብ ርቀት የምትገኝ መሆኗ ከሌሎች ወደብ አልባ አገራት ልዩ እንደሚያደርጋት የዓለም አቀፍ ተሞክሮን በማጣቀስ አብራርተዋል። ኢትዮጵያ ዘላቂ የተፈጥሮ ሀብትን በፍትሃዊነት መጠቀም በሚለው እሳቤ የምታምንና እሳቤውንም በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ላይ በተግባር ማሳየቷን ጠቅሰዋል። ይህም በመሆኑ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ከፍትሃዊ ተጠቃሚነት እሳቤ የሚመነጭና የህልውና ጉዳይ በመሆኑ በሁሉም ዘንድ ሊደገፍ ይገባል ሲሉ አስረድተዋል። የባህር በር ጥያቄው ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ መገንባት እንድትችል እና የህዝብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑንም ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ፍትሃዊ የባህር በር ጥያቄ የብሔራዊ ጥቅምና የህልውና ጉዳይ በመሆኑ ፍላጎቱን እውን ለማድረግ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ያሉት በዩኒቨርሲቲው የውኃና መስኖ የትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ አቶ ተስፋሁን አዲሱ ናቸው። ኢትዮጵያ ባለፉት 30 ዓመታት ፍትሀዊ ባልሆነ መንገድ ወደብ አልባ መሆኗ የሚያስቆጭ መሆኑን ጠቅሰው ኢትዮጵያ የባሕር በር ስለሌላት ብቻ በዓለም አቀፍ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ የገቢና ወጪ የንግድ ሥርዓት ውስጥ ለከፍተኛ ወጪ ስትዳረግ መቆየቷን አስታውስዋል። አሁን የጀመረችው ጥረት ከቀጣናው አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተሰሚነቷንና ተጽዕኖ ፈጣሪነቷን የሚያሳድግ በመሆኑ ጥያቄው በሁሉም ዘንድ ሊታገዝ ይገባል ብለዋል።
የዋጋ ንረትን የሚያረጋጉ አሠራሮች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Oct 15, 2025 66
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 5/2018(ኢዜአ)፡- 219 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ጨምሮ በአምሥት የገበያ ማዕከላት የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች አቅርቦት በበቂ ሁኔታ የማቅረቡ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገለጸ። የአዲስ አበባ ከተማ አሥተዳደር ንግድ ቢሮ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አሸናፊ ብርሃኑ እንዳሉት፤ 219 የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ጨምሮ በአምሥት የገበያ ማዕከላት የዋጋ ንረትን ያረጋጋ ግብይት እየተከናወነ ነው። ለእነዚህ ገበያዎችና ማዕከላት የግብርና እና ኢንዱስትሪ ምርት በበቂ ሁኔታ ከሥር ሥር እየቀረበ መሆኑንም ለኢዜአ አረጋግጠዋል። በየሳምንቱ እየወጣ ባለው የዋጋ ተመን መሠረት ግብይት እንደሚከናወንም አስረድተዋል። ከሌሎች ነጻ ገበያዎች አንጻር በቅዳሜና እሁድ እንዲሁም በአምሥቱ ገበያ ማዕከላት በአማካይ ከ20 በመቶ በላይ ቅናሽ ተደርጎ እንደሚሸጥም ተናግረዋል። በሁሉም የመዲናዋ ወረዳዎች የቅዳሜና እሁድ ገበያ መኖሩን ጠቅሰው፤ ከፍላጎት ማደግ አንጻር በቀጣይ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን የማስፋት ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን አመላክተዋል። በዚህም መሰረት አንድ የቅዳሜና እሁድ ገበያ ስፍራ ባላቸው ወረዳዎች ተጨማሪ እንዲኖር ይደረጋል ብለዋል። እነዚህ የገበያ አማራጮች በተቀመጠው አሠራር መፈጸማቸውን የሚከታተሉ ሱፐር ቫይዘሮች መመደባቸውን እና 1 ሺህ 216 የግብይት ተቆጣጣሪዎች በስምሪት ላይ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ሕገ ወጥ ድርጊት ሲፈጽሙ የተገኙ የቅዳሜና እሁድ ገበያ ሻጮች ከትስስር ውጭ እንደሚደረጉ እና በሕግም ተጠያቂ እንደሚሆኑ አስገንዝበዋል።
የንጋት ሐይቅ የተቀናጀ ማስተር ፕላን ዝግጅት የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ትሩፋቶችን በሚገባ መምራት የሚያስችል ነው
Oct 14, 2025 170
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 4/2018(ኢዜአ)፦ የንጋት ሐይቅ የተቀናጀ አስተዳደርና አጠቃቀም ማስተር ፕላን ዝግጅት የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ትሩፋቶችን በሚገባ መምራት የሚያስችል መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና የአካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ(ዶ/ር) ገለጹ። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሃብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) በበኩላቸው የኢትዮጵያን የዘመናት ፍትሐዊ የውሃ ሃብት የመጠቀም መብት በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ስኬት ማረጋገጥ እንደተቻለ ገልጸዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ - የንጋት ሐይቅ የረቂቅ ማስተር ፕላን ጥናት ማስጀመሪያ የምክክር መድረክ በቢሾፍቱ ከተማ ተካሂዷል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና የአካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ(ዶ/ር)፤ የንጋት ሐይቅ የተቀናጀ አስተዳደርና አጠቃቀም ማስተር ፕላን ዝግጅት የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ትሩፋቶችን በሚገባ መምራት የሚያስችል ነው ብለዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ከሚያመነጨው የኤሌክትሪክ ኃይል ባለፈ በዓሳ ሃብት፣ ቱሪዝምና ትራንስፖርት መስክ የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በዕቅድ መምራት እንደሚኖርባቸው አስገንዝበዋል። ምክር ቤቱም የንጋት ሰው ሰራሽ ሐይቅን ጨምሮ የዓባይ የውሃ ተፋሰስ ደኅንነትን የሚያስጠብቁ የህግ፣ የፖሊሲ ማዕቀፍ ዝግጅት ጉዳዮች ላይ ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን አስታውቀዋል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሃብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር)፤ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግደብ መመረቅ የዜጎች ትልቅ የኩራት ምንጭ መሆን መቻሉን ገልጸዋል። በዚህም የኢትዮጵያን የዘመናት ፍትሐዊ የውሃ ሃብት የመጠቀም መብት በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ስኬት አረጋግጠናል ብለዋል። ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ዜጎች የዘመናት በውሃ ሃብታቸው የመጠቀም ቁጭትን በተባበረ ክንድ ምላሽ በመስጠት ዘርፈ ብዙ ትሩፋት ማግኘት የቻሉበት መሆኑን ተናግረዋል። የግድቡ የኃይል አቅርቦትም ከሀገር ባሻገር ቀጣናዊ የትስስር አቅምን በማሳደግ ትልቅ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እየፈጠረ እንደሚገኝ አንስተዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ የፈጠረውን የንጋት ሰው ሰራሽ ሐይቅ ዘርፈ ብዙ ትሩፋት በሥርዓት ማስተዳደር የሚያስችል ማስተር ፕላን እየተዘጋጀ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጌታሁን አብዲሳ፤ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ በኢትዮጵያውያን አንጡራ ሀብት የተገነባ የማድረግ አቅማችንና የአንድነታችን መገለጫ ነው ብለዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ከሚሰጠው የኃይል አቅርቦት ባሻገር የንጋት ሐይቅ ለኢትዮጵያውያን ዘርፈ ብዙ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ጸጋዎችን ይዞ መምጣቱን ገልጸዋል። የንጋት ሐይቅና የአካባቢው አስተዳደር ማስተር ፕላን ዝግጅትም ሐይቁ የፈጠራቸውን ጸጋዎች በተቀናጀ ሥርዓት ለማስተዳደር ትልቅ ትርጉም የሚሰጠው መሆኑን ተናግረዋል። በንጋት ሐይቅ የረቂቅ ማስተር ፕላን ጥናት ማስጀመሪያ የምክክር መድረክ ላይ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።