ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ደህንነትን በማረጋገጥ ለግንባታው አስተዋጽኦ እያደረግን ነው - የመከላከያ ሠራዊት አመራሮችና አባላት
Jun 14, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ደህንነትን በማረጋገጥ ለግንባታው በተለያየ መልኩ አስተዋጽኦ እያደረገን ነው ሲሉ የመከላከያ ሠራዊት አመራሮችና አባላት ገለጹ። የመላው ኢትዮጵያውያን አሻራ ያረፈበት ታላቁ ሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ ደረጃ ላይ መድረሱ እንዳስደሰታቸውም ተናግረዋል። በምዕራብ ዕዝ የ404 ሕዳሴ ኮር ሶስተኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን "ሕዳሴን በሕዳሴ ኮር" በሚል መሪ ሐሳብ በተለያዩ ዝግጅቶች በማክበር ላይ ይገኛል። የሠራዊቱ አባላትም በዛሬው ዕለት ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ጎብኝተዋል። በጉብኝታቸውም የመላው ኢትዮጵያውያን አሻራ ያረፈበት ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ወደ መጠናቀቁ ደረጃ ደርሶ በመመልከታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። የምዕራብ ዕዝ ምክትል አዛዥ ሜጀር ጄኔራል ሙላቱ ጀልዴ በጉብኝቱ ወቅት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ወደ መጠናቀቁ ደረጃ ለመድረሱ መላው ኢትዮጵያውያን ያላሰለሰ ጥረት ማድረጋቸውን ተናግረዋል። መከላከያ ሠራዊቱ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ እውን እንዲሆን የግድቡን ደህንነት ከማስጠበቅ ጀምሮ የሚጠበቅባቸውን ሁሉ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ገልጸዋል። በምዕራብ ዕዝ የሪጅን ሶስት ኮር ዋና አዛዥ ብርጋዴር ጄኔራል ዘመኮንን አበራ እንደገለጹት፤ ሠራዊቱ የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅና ግዳጁን በብቃት ለመወጣት ከምን ጊዜውም በላይ ዝግጁ ነው። ሕዳሴ ኮር የግድቡን አካባቢ ሰላምና ጸጥታ ለማስከበር እያደረገ ያለውን ተግባር በውጤታማነት እየተወጣ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህንን ተግባሩን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በምዕራብ ዕዝ የ403 ኮር አባል ሌተናል ኮሎኔል ፍሰሃ ጥላሁን በበኩላቸው እንደገለጹት፤ የታላቁ የህዳሴ ግድብ የመላው ኢትዮጵያውያን እስትንፋስ በመሆኑ ሠራዊቱ ሁሌም የአካባቢውን ሰላም በማስጠበቅ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ታላቁ የሕደሴ ግድብ አሁን የደረሰበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ ሠራዊቱ አስፈላጊውን ሁሉ ማበርከቱን ጠቁመዋል። ዛሬ ለደረሰበት የመጠናቀቅ ደረጃ ደርሶ በመመልከታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል። በምዕራብ ዕዝ የ403 ኮር አባል ሌተናል ኮሎኔል ቴዎድሮስ ዘመነ እንዳሉትም፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያውያን የይቻላል መንፈስ ማሳያ ነው። ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ለሀገር በረከት የመሆን ደረጃ ላይ በመድረሱ መደሰታቸውን ጨምረው ተናግረዋል።
ሴቶች በኮንስትራክሽን ዘርፍ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ የባለድርሻ አካላት ቅንጅት ወሳኝ ነው
Jun 14, 2025 47
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ ሴቶች በኮንስትራክሽን ዘርፍ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን አስታወቀ። ኮርፖሬሽኑ ”ኢትዮጵያ ትገንባ” በሚል መሪ ሀሳብ ሴቶች በኮንስትራክሽን ዘርፉ ያላቸው ተሳትፎ ማዳበር በሚቻልበት ሁኔታዎች ላይ የሚመክር ኮንፍረንስ ተካሂዷል። በመድረኩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሴት አመራሮች እንዲሁም መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት አመራሮች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን ፅህፈት ቤት ሃላፊ ቤዛዊት ግርማ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት በኢትዮጵያ ሴቶች በተለያዩ የግንባታ ፕሮጀክቶችና መሰረተ ልማት ዝርጋታ ስራዎች ጉልህ ሚና እየተወጡ ይገኛሉ። በአሁኑ ወቅትም ዘርፉ በቴክኖሎጂ እያደገ በመምጣቱ በአገሪቱ የልማት ጉዞ ላይ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። ኮርፖሬሽኑ በተለያዩ ህጎች ላይ ማሻሻያዎችን በማድረግና ስትራቴጂዎችን በመንደፍ ሴቶች በዘርፉ ያላቸውን ተሳትፎ ከፍ ለማድግ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ሴቶች በግንባታ ዘርፍ ያለውን እድልና ቴክኖሎጂ በመጠቀም እውቀታቸውንና ክህሎታቸውን በማዳበር ወደ ዘርፉ በስፋት መግባት እንዳለባቸውም አስታውቀዋል። ሴቶች በኮንስትራክሽን ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ እንደሚገባ ነው ዶክተር ቤዛዊት ያስታወቁት። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የከተማ መሰረተ ልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል ፍቅር አባይ በዚሁ ግዜ በአገሪቱ በሚከናወኑ ትላልቅ ፕሮጀክቶች ላይ የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባ አመልክተዋል ። ይህንንም ለማጠናከር የህግና ፖሊሲ ክፍተቶች ከመሙላት አኳያ የሁሉም ባለድርሻ አካላት ርብርብ እንደሚያስፈልገው ጠቁመዋል። በኮንስትራክሽን ስራ ላይ የተሰማሩ መንግስታዊና የግል ድርጅቶችም የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ ወሳኝ ድርሻ አላቸው ያሉት ደግሞ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ጉዳይ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ነጭቴ ፍላቴ ናቸው። የሴቶችን እኩል ተሳታፊነት የተመለከቱ ረቂቅ አዋጆች ፀድቀው ወደ ስራ እንዲገቡ የድርሻቸው እንደሚወጡም ተናግረዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልና በመድረኩ ጥናት ያቀረቡት ደጅይጥኑ አለነ እንዳሉት ሴቶችን በኮንስትራክሽን ዘርፍ ያላቸው ተሳትፎ ለማሳደግ አቅዶ መንቀሳቀስ እንደሚያስፈልግ ገልፀዋል። በሀገሪቱ እየተከናወኑ በሚገኙ የኮሪደር ልማት የሴቶች ተሳትፎ የተሻለ በመሆኑ ይህም ለሌሎች ዘርፎች ተሞክሮ የሚሆን ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ የምታስተናግዳቸው ኮንፍረንሶች መልካም ገጽታን ከማስተዋወቅ ባሻገር የዲፕሎማሲ ግንኙነቶችን ለማጠናከር የሚያግዙ ናቸው
Jun 14, 2025 50
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የምታስተናግዳቸው አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ኮንፍረንሶች የሀገሪቱን መልካም ገጽታ ከማስተዋወቅ ባሻገር የዲፕሎማሲ ግንኙነትን የበለጠ ለማጠናከር እንደሚያግዙ ተገለጸ። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢትዮጵያ በተለይም በአዲስ አበባ በርካታ ዓለም አቀፍና አህጉራዊ ኮንፍረንሶች በስፋት እየተካሄዱ ይገኛሉ። የአዲስ አበባ ከተማን የዲፕሎማቲክ መቀመጫነትና የአፍሪካ መዲናነት የሚመጥኑ መሰረተ ልማቶች መሟላት ደግሞ ለኮንፍረንስ ቱሪዝም መበራከት ምቹ ሁኔታን የፈጠሩ ናቸው። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን ተከትሎ የተለያዩ ዘርፎች ለውጭ ባለሃብቶች ክፍት መደረጉም ሌላው እድል ነው። ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎችም ይህንኑ ነው የሚያረጋግጡት። በፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት መሪ ተመራማሪ አማረ ቀናው(ዶ/ር)፤ ከተማዋ የምታስተናግዳቸው ዓለም አቀፋዊና አህጉራዊ ስብሰባዎች ከሀገር በጎ ገጽታ ግንባታ ያለፈ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ አላቸው። የኢትዮጵያን የውጭ ጉዳይ ፖሊሲና የዲፕሎማሲ ስራ ለሀገር ወስጥም ሆነ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለማድረስ እንደሚያግዙ ተናግረዋል። በቱሪዝም ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን መሪ ስራ አስፈጻሚ አለማየሁ ጌታቸው፤ ኢትዮጵያ እየገነባቻቸው ያሉ የተለያዩ መሰረተ ልማቶችና የቱሪዝም መስህቦቿ ለኮንፍረንስ ቱሪዝም ተመራጭ እንዳደረጓት ይገልጻሉ። የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎችና የሌሎች መሰረተ ልማቶች መሟላት አዲስ አበባን ለኮንፍረንስ ቱሪዝም የበለጠ ምቹና ተመራጭ እንድትሆን ማስቻላቸውን ተናግረዋል። ወደ ሀገሪቱ የሚመጡ የውጭ ዜጎች ስለኢትዮጵያ የቱሪዝም መዳረሻዎችና ባህላዊ እሴቶች በቂ ግንዛቤ እንዲይዙ በሚካሄዱ ኮንፍረንሶች ገለጻ እየተደረገ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ በተያዘው ዓመት ከተካሄዱ ዓለም አቀፍና አህጉራዊ ኮንፍረንሶች አራቱ በኢትዮጵያ ሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ መዘጋጀታቸውን የገለጹት ደግሞ የጉባዔው ጠቅላይ ፀሐፊ ቀሲስ ታጋይ ታደለ ናቸው። እርሳቸው እንደሚሉት፤ ኢትዮጵያ ከራሷ አልፎ ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ ያላትን ተሳትፎ የበለጠ ለማሳደግ ኮንፍረንሶቹ ዕድል የፈጠሩ ናቸው ብለዋል። የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የባለድርሻ አካላት ዳይሬክተር ሳሚናስ ሰይፋ፤ ተቋሙ በቅርቡ ዓለም አቀፉን የአይዲ ፎር አፍሪካ ጉባዔ በተሳካ ሁኔታ ማካሄዱን አስታውሰዋል። የተለያዩ ኮንፍረንሶችን ለመሳተፍ የሚመጡ እንግዶችን የቆይታ ጊዜ የሚያራዝሙ በርካታ ሥራዎች መሰራታቸውንና በቱሪዝም ዘርፍ የተሻለ አቅም መፈጠሩንም ተናግረዋል። በፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት መሪ ተመራማሪ አማረ ቀናው(ዶ/ር) በበኩላቸው ኢንስቲትዩቱ ኮንፍረንሶቹ ላይ የሚነሱ ሀሳቦች ለፖሊሲ ግብዓት እንዲሆኑ የኮንፍረንሶቹን ጭብጦች በህትመት መልክ እንዲሰራጩ የሚያደርግ መሆኑንም ተናግረዋል።
የወጣቶችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ተግባራትን ይበልጥ ማጠናከር ይገባል - ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀስላሴ
Jun 14, 2025 80
ጊንጪ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ የወጣቶችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ተግባራትን ይበልጥ አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀስላሴ ገለጹ። በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ጊንጪ ከተማ አቅራቢያ የተገነባው 'ኬኛ ቢቨሬጅስ' ፋብሪካ ዛሬ ተመርቆ አገልግሎት ጀምሯል። በምረቃ ሥነ-ሥርዓት ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀስላሴ፣ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሸመልስ አብዲሳን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀስላሴ፤ የልማት ስራዎች የወጣቱን ተጠቃሚነት ማዕከል ያደረጉ መሆን እንዳለባቸው ተናግረዋል። ዛሬ የተመረቀው ፋብሪካም ለአካባቢው ማህበረሰብ ትልቅ በረከት መሆኑን ጠቅሰው፤ ከጥሬ እቃ አቅርቦት ጀምሮ ትልቅ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ አለውም ብለዋል። በተለይ የግብርና ዘርፉን ከማሳደግ አንጻር ፋይዳው የጎላ መሆኑን አንስተዋል። ይህም በመሆኑ ለወጣቶች ስራ የሚፈጥሩ እና የወጣቱን ተጠቃሚነት ማዕከል ያደረጉ የልማት ተግባራትን ይበልጥ ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ በበኩላቸው፤ በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የልማት ተግባራት ወጣቶችን በስፋት ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። የክልሉ መንግስት አሰራሮችን በማሻሻል እና ህዝቡን በስፋት በማሳተፍ አበረታች የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ ያለውን የልማት አቅም በመጠቀም የህዝብን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አንስተዋል። በተለይም ወጣቶች ስራ እንዲያገኙና በንቃት እንዲሳተፉ ዕድል የፈጠሩ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። ዛሬ የተመረቀው ፋብሪካ የዚሁ ጥረት ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው፤ መሰል ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። ፋብሪካው በክልሉ ምዕራብ ሸዋ ዞን በ110 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ ሲሆን፤ 22 ቢሊዮን ብር ኢንቨስት የተደረገበት መሆኑም ታውቋል። ፋብሪካው ከ4ሺህ በላይ ባለአክሲዮኖች የተቋቋመ፣ ከ250 ለሚበልጡ ዜጎች የስራ ዕድል ያገኙበትና እና በእሴት ሰንሰለቱ መሰረት ለ1ሺህ ዜጎች የስራ ዕድል እንደሚፈጥር ተመልክቷል።
የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት በሌሎች ተቋማት እንደ አርዓያ የሚወሰድ ተግባር ነው
Jun 14, 2025 37
ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት በሌሎች ተቋማት እንደ አርዓያ የሚወሰድ ተግባር እያከናወነ መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግ እና ፍትህ ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ኢሳ ቦሩ አመለከቱ። የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት በ2017 በጀት ዓመት ባከናወናቸው ውጤታማ ተግባራትና ያጋጠሙ ተግዳሮቶችን በተመለከተ ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግ እና ፍትህ ቋሚ ኮሚቴ አባላት ጋር ውይይት አድርጓል። በውይይቱም የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ ኢሳ ቦሩ እንዳሉት፣ የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ገልፀዋል። በዚህም ተገልጋዩ ጥራት ያለው አገልግሎት እያገኘ መሆኑን ጠቁመው በተለይም ከለውጡ በፊት የአገልግሎት ሰጪ ተቋማቱ የህዝብ እሮሮ የሚሰማባቸውና የአገልግሎት አሰጣጥ ችግር የሚስተዋልባቸው እንደነበሩ አስታውሰዋል። ሆኖም የለውጡ መንግስት በአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ላይ በወሰደው የማሻሻያ ሪፎርሞች ስራዎች በርካታ ለውጦች መታየታቸውን ጠቁመዋል። በዚህም በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት በመስጠት ለሌሎች ተቋማት እንደአርዓያ የሚወሰድ አገልግሎት እንዲሰጥ ምክንያት መሆኑን አንስተዋል። የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሃሚድ ኪኒሶ በበኩላቸው፣ ተቋሙ ከምንጊዜውም በላይ አገልግሎቱን እያሰፋ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ለዚህም ተቋሙ ዘመኑን የዋጁ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ጥቅም ላይ በማዋል ረጅም ወረፋ በመያዝ ለደንበኞች እንግልት ይፈጥር የነበረውን አሰራር በኦንላይን በማድረግ የተገልጋዩን እርካታ መጨመር መቻሉን ገልፀዋል። በዚህም በቀን በአማካይ ከስድስት ሺህ በላይ ደንበኞችን እንደሚያስተናግድ ገልፀው ከመንግሥት የስራ ሰዓት ውጪ የምሳ ሰዓትን እንዲሁም እስከ ምሽቱ አንድ ሰዓት አገልግሎቶች እየተሰጡ እንደሚገኝ ተናግረዋል። እንደ ዋና ዳይሬክተሩ ገለፃ፣ ሀሰተኛ ሰነዶችን የሚያጋልጡና የተለያዩ የማጭበርበር ተግባራትን መከላከል የሚያስችሉ የተለያዩ አዳዲስ አሰራሮች ወደ ትግበራ መግባታቸውንም አብራርተዋል። የፋይዳ መታወቂያን እንደ ቅድመ ሁኔታ በማስቀመጣችን ማንነትን መሰረት ተደርጎ ይሰራ የነበረውን ማጭበርበር ማስቀረት ተችሏል ብለዋል።
በብሔረሰብ አስተዳደሩ በ71 ትምህርት ቤቶች የጓሮ አትክልት ልማት የሰርቶ ማሳያ ተግባር እየተከናወነ ነው
Jun 14, 2025 51
ሰቆጣ ፤ሰኔ 7/2017 (ኢዜአ)፡- በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በ71 ትምህርት ቤቶች ስርዓተ ምግብን ለማጎልበት የሚያስችሉ የጓሮ አትክልት ልማት ሰርቶ ማሳያ እየተከናወነ መሆኑን የብሔረሰብ አስተዳደሩ ትምህርት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ፍትሃለሽ ምህረቴ ለኢዜአ እንደገለፁት በብሔረሰብ አስተዳደሩ የሚስተዋለውን የስርዓተ ምግብ ችግርን ለመቅረፍ ሁሉን አቀፍ ጥረት እየተደረገ ነው። በዚህም በትምህርት ቤቶች ላይ የምገባ መርሃ ግብር በማካሄድ ህጻናት በቂ ምግብ አግኝተው ትምህርታቸውን እንዲከታተሉና ውጤታማ እንዲሆኑ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪም በ71 ትምህርት ቤቶች የስርዓተ ምግብ የጓሮ አትክልት ልማት በማካሄድ የስርዓተ ምግብ ችግርን ለመቅረፍ እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በትምህርት ቤቶች እየተካሄደ ያለው የጓሮ አትክልት ልማት ክበባትን በማቋቋም ተማሪዎች በቀጣይ በቤታቸውም እንዲተገብሩት ግንዛቤ መፍጠር ጀምሮ ሌሎች እገዛዎች እየተደረጉ ነው ብለዋል። የትምህርት ቤቶች ባላቸው ክፍት መሬት ተጠቅመው የጓሮ አትክልት በማልማት ለማህበረሰቡ ሞዴል በመሆን የተመጣጠነ ምግብ እጥረት የሚፈጥረውን ችግር ለመቅረፍ አልመው መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል። በዞኑ በጋዝጊብላ ወረዳ የመስቀሎ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር ስለሽ ጌታሁን እንዳሉት በትምህርት ቤታቸው እየተከናወነ ያለው የአትክልት ልማት ለሌላው ማህበረሰብ እንደ ተሞክሮ የሚወሰድ ነው። ወደ ማህበረሰቡ ለማስፋትም 30 ተማሪዎች አባል የሆኑበት የስርዓተ ምግብ ክበብ በመመስረት የጓሮ አትክልት ልማትን በቤታቸውና በአካባቢያቸው እንዲያካሄዱ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በትምህርት ቤቱ የስርዓተ ምግብ ክበብ አባል የሆነችው ተማሪ ጤና ታደሰ፤ በትምህርት ቤቱ በክበባቸው አማካኝነት የጓሮ አትክልት እያለሙ መሆናቸውን ተናግራለች። ''ክበቡ የስርዓተ ምግብ ግንዛቤን ከማስጨበጥ ባለፈ በቤታችን የጓሮ አትክልትን በማልማት እንድንመገብ አስችሎናል።'' ብላለች።
ሴቶች በግንባታ ዘርፍ ያለውን እድልና ቴክኖሎጂ በመጠቀም ወደ ዘርፉ በስፋት እንዲገቡ ተጠየቀ
Jun 14, 2025 41
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ ሴቶች በግንባታ ዘርፍ ያለውን እድልና ቴክኖሎጂ በመጠቀም ወደ ዘርፉ በስፋት እንዲገቡ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን ጥሪ አቀረበ። ኮርፖሬሽኑ ”ኢትዮጵያ ትገንባ” በሚል መሪ ሀሳብ ሴቶች በኮንስትራክሽን ዘርፉ ያላቸው ተሳትፎ በሚዳብርበት ሁኔታ ላይ የሚመክር ኮንፍረንስ እያካሄደ ይገኛል። በመድረኩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሴት አመራሮች እንዲሁም መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት አመራሮች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን ፅህፈት ቤት ሃላፊ ቤዛዊት ግርማ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት ኮርፖሬሽኑ ሴቶች በዘርፉ ያላቸውን ተሳትፎ ከፍ ለማድረግ በተለያዩ ህጎች ላይ ማሻሻያዎች በማድረግና ስትራቴጂዎችን በመንደፍ እየተሰራ ይገኛል። ኮርፖሬሽኑ ተግባራዊ ካደረጋቸው የሪፎርም ስራዎች መካከልም ስርዓተ ፆታን ማካተትና የሴቶችን ተሳትፎ ማሳደግ አንዱ መሆኑን አንስተዋል። በተጨማሪም ሴቶችን ያማከሉ የተለያዩ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች በመስጠትና የትምህርት ዕድል በማመቻቸት የማብቃት ስራዎች እንደተሰሩም ተናግረዋል። ሴቶች በግንባታ ዘርፍ ያለውን እድልና ቴክኖሎጂ በመጠቀም እውቀታቸውንና ክህሎታቸውን ይበልጥ በማዳበር ወደ ኮንስትራክሽን ዘርፉ በስፋት እንዲገቡም ጠይቀዋል።
የከተማዋ ነዋሪዋች በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በመሰማራት ተጠቃሚ ሆነዋል
Jun 14, 2025 41
ቡታጅራ ፤ሰኔ 7/2017 (ኢዜአ)፡-በቡታጅራ ከተማ አስተዳደር በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በእንስሳት እርባታና በአትክልትና ፍራፍሬ ምርት ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን ነዋሪዎች ተናገሩ ። የቡታጅራ ከተማ አስተዳደር በበኩሉ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የነዋሪዎችን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት ትኩረት እንደተሰጣቸው ነው ያመለከተው። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት "የእኛ ለእኛ የወተት እርባታ ማህበር" ሰብሳቢ አቶ ሳህሌ መኮንን እንደገለጹት፤ ለአምስት ተደራጅተው በሁለት የወተት ላሞች ስራ ከጀመሩ ሁለተኛ ዓመት እንደሆናቸውና የተሻለ ገቢ ወደ ማግኘት እየተሸጋገሩ ነው ። አስተዳደሩ ባመቻቸው የመስሪያ ቦታና መነሻ ብድር እና የህይወት ክህሎት ስልጠና በመታገዝ ገቢያቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረው ማህበሩ ከአባላቱ ጥቅም አልፎ ለሌሎች የስራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚ ማድረግ መጀመሩን ገልጸዋል። ሌላኛውና ለሶስት ተደራጅተው በእንቁላልና ስጋ ዶሮ እርባታ ስራ ላይ የተሰማሩት "የቤተሰብ የዶሮ እርባታ ማህበር" ሰብሳቢ ኡስማን ሳቢር በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በተደረገላቸው ድጋፍ ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም የእንቁላልና የሥጋ ዶሮዎችን በማርባት ለገበያ በማቅረብ ውጤታማ እየሆኑ እንደሚገኙና የገበያ ትስስር እንደተፈጠረላቸውም አስረድቷል። ከዚህም ባለፈ ባላቸው ውስን ቦታ አትክልት እና ፍራፍሬ እያለሙ መሆኑን ገልፀው በስራቸው ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል። መምህር ጀንበር ፈለቀ በበኩላቸው ከሌሎች ባገኙት ልምድ ከመምህርነት ሙያቸው ጎን ለጎን ፍየልና በግን በማሞከት ተግባር ላይ ተሰማርተው ህይወታቸውን እየቀየሩ ነው። የቡታጅራ ከተማ ከንቲባ አቶ አብዱ አህመድ በበኩላቸው በከተማዋ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ተደራጅተው የተሰማሩ ዜጎች ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረው ዘርፉን ለማጠናከርም መንደር የመፍጠር ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በከተማዋ 23 የዶሮ፣ 21 የወተት እንዲሁም 3 የንብ መንደሮች መፈጠራቸውን ከንቲባው አውስተዋል። በማህበር በመደራጀት በተቀናጀ መንገድ ወደ ስራ የገቡ ዜጎች በሚደረግላቸው ድጋፍ ታግዘው ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች የስራ ዕድል እየፈጠሩ እንዳሉም ጠቁመዋል። ይህን ለማጠናከርም የብድር፣ የቦታና የክህሎት ማሳደጊያ ስልጠና ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ ነው ብለዋል ከንቲባው። እንዲሁም ዝርያቸው የተሻሻሉ የወተት ላሞች፣ ዶሮ እና የአሳ ጫጩት በዘርፉ ለተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች እየተሰራጩ መሆናቸውን አመልክተዋል። በተጨማሪም የማር ምርት ለማሳደግ ዘመናዊ ቀፎዎችን የማቅረብ ስራም እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። የሌማት ትሩፋት ከኢኮኖሚ ምንጭነት፣ ከምግብ ፍጆታነትና ገበያን ከማረጋጋት ባለፈ በስነ-ምግብ ረገድ እየተጫወተ ያለውን ጉልህ ሚና ለማጠናከር የሚደረጉ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል።
በጊንጪ ከተማ አቅራቢያ የተገነባው ኬኛ ቢቨሬጅ ፋብሪካ ተመረቀ
Jun 14, 2025 92
ጊንጪ ፤ሰኔ 7/2017 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ምእራብ ሸዋ ዞን ጊንጪ ከተማ አቅራቢያ የተገነባው ኬኛ ቢቨሬጅ ፋብሪካ ተመርቆ አገልግሎት ጀመረ። በፋብሪካው ምረቃ ላይም የኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀስላሴ እና የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሸመልስ አብዲሳን ጨምሮ የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል። ፋብሪካው በክልሉ ምእራብ ሸዋ ዞን በ110 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈ ሲሆን 22 ቢሊዮን ብር መዋዕለ ንዋይ ፈሰስ የተደረገበት መሆኑም ታውቋል። ፋብሪካው ከ4 ሺህ በላይ ባለ አክሲዮኖች የተቋቋመና ከ250 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች በቀጥታ የስራ እድል የፈጠረ መሆኑም ተመላክቷል። እንዲሁም በምርት አቅርቦትና በሌሎች የእሴት ሰንሰለት ለ1 ሺህ ዜጎች በተዘዋዋሪ የስራ እድል ተጠቃሚ እንደሚያደርግም ታውቋል።
የህብረት ስራ ማህበራት አሰራራቸውን በማዘመን ተወዳዳሪና ገበያ ተኮር እንዲሆኑ ጥረት እየተደረገ ነው - ኮሚሽኑ
Jun 13, 2025 54
ሆሳዕና፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ የህብረት ስራ ማህበራት አሰራራቸውን በማዘመን ተወዳዳሪና ገበያ ተኮር እንዲሆኑ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የኢትዮጵያ ህብረት ስራ ኮሚሽን ገለፀ፡፡ "የህብረት ስራ ማህበራት ሚና ለዜጎች ሁለንተናዊ ብልፅግና!" በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ 2ኛው ዙር የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሲምፖዝየም፣ ኤግዚቢሽንና ባዛር የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው በተገኙበት በሆሳዕና ከተማ ተካሂዷል፡፡ የኢትዮጵያ ህብረት ስራ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ሺሰማ ገብረስላሴ በዚህ ወቅት እንዳሉት የህብረት ስራ ማህበራት ያላቸውን አቅም አሟጠው መጠቀም እንዲችሉ የአሰራር ማሻሻያ እያደረጉ ነው። ህብረት ስራ ማህበራቱ የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲወጡ ከማስቻል አኳያ ያሉባቸውን ችግሮች የመለየት ስራ መሰራቱን ገልጸው በተለዩ ችግሮች ዙሪያ በተሰራው ሪፎርም በርካታ የህብረት ስራ ማህበራት ዳግም በማንሰራራት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል። የህብረት ስራ ማህበራት አሰራርን በማዘመን ማህበራቱን ተወዳዳሪና ገበያ ተኮር ለማድረግ የተጀመረው ጥረት እንደሚጠናከርም ገልጸዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ኃላፊ ኡስማን ስሩር፤ የህብረት ስራ ማህበራት በተለይ ግብርናን ከማዘመን አንጻር አበረታች ስራ እየሰሩ ነው። በተጨማሪም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ፈጣን ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከማምጣት አኳያ ጉልህ አስተዋጽኦ በማበርከት ላይ ይገኛሉ ብለዋል፡፡ በክልሉ የህብረት ስራ ማህበራትን በማጠናከር የማህበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራም ገልፀዋል፡፡ የክልሉ ህብረት ስራ ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ተመስገን ጎዴቦ በበኩላቸው በክልሉ የሚገኙ የህብረት ስራ ማህበራት ምርቶቻቸውን እንዲያስተዋውቁ እና ትስስር እንዲፈጥሩ ኤግዚቢሽንና ባዛሩ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። በክልሉ የህብረት ስራ ማህበራትን ለማጠናከር በተጀመሩ የሪፎርም ስራዎች ተስፋ ሰጪ ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞንና የልዩ ወረዳ እና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮችና የህብረት ስራ ማህበራት አባላትና አመራሮች ተሳትፈዋል፡፡
በክልሉ በግብርናው መስክ የተገኙ ውጤቶችን በማስቀጠል የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Jun 13, 2025 71
ሀዋሳ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በግብርናው መስክ የተገኙ ውጤቶችን በማስቀጠል የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ የ2017/18 የምርት ዘመን የመኸር ወቅት የንቅናቄ መድረክ በሀዋሳ አካሂዷል። በመድረኩ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ እንደገለጹት የክልሉ መንግስት በግብርናው መስክ የተገኙ ውጤቶችን በማስቀጠል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ ነው። በዘርፉ ባለፉት አመታት የተገኙ ተሞክሮዎችን በመቀመርና ልማቱን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍ ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በዘንድሮ የመኽር ወቅትም እንደ ክልል የተያዙ እቅዶችን ለማሳካት የተጀመሩ ተግባራትን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የክልሉ መንግስት የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ከቀረጻቸው ፓኬጆች 19ኙ በግብርናው ዘርፍ የሚተገበሩ በመሆናቸው አመራሩ በመቀናጀትና በሃላፊነት ሊመራው እንደሚገባ አሳስበዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ ሃላፊ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው በዘንድሮው የመኸር ወቅት ከ159ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት እቅድ መያዙን ገልጸዋል። በዚህም ከ20 ሚሊየን ኩንታል በላይ የዋና ዋናና የስራስር ሰብሎች ምርት እንደሚጠበቅ ገልጸው እቅዱ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር 20 በመቶ ብልጫ አለው ብለዋል። በምርት ዘመኑ ከተያዘው የመሬት ሽፋን ከፍተኛው በዋና ዋና ሰብሎች እንደሚሸፈን አመላክተዋል። የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጡ የስራስር ሰብሎችን የማስፋፋትና እንደ ክልል የቤተሰብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ በእርሻው ዘርፍ የተያዙ ፓኬጆችን ለማሳካት ትኩረት ይደረጋል ብለዋል። ለዚህም በቂ ቅድመ ዝግጅት መደረጉን ጠቅሰው ለምርት ወቅቱ ለክልሉ ከተያዘው 300ሺህ ኩንታል ማዳበሪያ እስካሁን 167ሺህ ኩንታሉ መግባቱን ገልጸዋል። በቂ የምርጥ ዘር ዝግጅችና አሲዳማ አፈርን ማከም የሚያስችል 80ሺህ ኩንታል ኖራ መዘጋጀቱንም ተናግረዋል። የዛሬው የንቅናቄ መድረክም በየደረጃው ያለው አመራር በእቅዱ ዙሪያ የጋራ መግባባት እንዲፈጥርና የተቀናጀ ድጋፍና ክትትል እንዲያደርግ ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን አመልክተዋል። በመድረኩ ርዕሰ መስተዳድሩን ጨምሮ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት የተገኙ ሲሆን በመኸር ልማት እቅዱና የትኩረት አቅጣጫዎች ባተኮሩ ሰነዶች ላይ ውይይት ተደርጓል።
በኦሮሚያ ክልል በ400 ሺህ ሄክታር አዲስ መሬት ላይ የቡና ችግኝ ይተከላል
Jun 13, 2025 73
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል በክረምቱ ወራት በ400 ሺህ ሄክታር አዲስ መሬት ላይ የቡና ችግኝ ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ የግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የቡናና ሻይ ዘርፍ ኃላፊ መሐመድ ሰኒ አሚን እንዳሉት በክልሉ የቡና ልማት በየጊዜው እየተስፋፋ ይገኛል። በዚህም ለዘንድሮ ክረምት የቡና ምርጥ ዘር ችግኝ በብዛትና በጥራት ለመትከል የሚያስችል አስፈላጊ ዝግጅት ሲደረግ መቆየቱን ገልጸዋል። የቡና ችግኝ ተከላው በስፋት የሚካሄደው በክልሉ ቡና አብቃይ አካባቢዎች ሲሆን በኩታ ገጠም እንደሚለማና ተከላው በዋናነትም በ18 ዞኖች ውስጥ እንደሚከናወን ጠቅሰዋል። በዚህም በክልሉ በ400 ሺህ ሄክታር ተጨማሪ አዲስ መሬት ላይ የቡና ችግኝ ለመትከል ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የችግኝ ተከላው እንደየአከባቢው ሁኔታ እንደሚካሄድ ገልጸው በሄክታር ከ2 ሺ 500 እስከ 3 ሺህ 300 በላይ ችግኝ የሚተከል መሆኑን አስረድተዋል። አሁን ላይ አንዳንድ አካባቢዎች የቡና ችግኝ ተከላው እየተከናወነ መሆኑን እና አርሶ አደሩ በስፋት እየተሳተፈ እንደሚገኝ ጠቅሰው ድጋፍና ክትትልም እየተደረገላቸው ይገኛል ብለዋል። በክልሉ ባለፉት 6 ዓመታት በሁለት ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ የነበረው የቡና ሽፋን አሁን ላይ ወደ ሶስት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ሄክታር መድረሱን ገልጸዋል። በተመሳሳይም በክልሉ በ7 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የሻይ ችግኝ ለመትከል የመሬት ልየታ እና ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የሻይ ልማቱም የሚካሄደው በጅማ፣ በኢሉአባቦር እና በቡኖ በደሌ ዞኖች ውስጥ መሆኑን ጠቅሰው ተከላው በኩታገጠም የሚከናወን እንደሆነም አስረድተዋል። በሌላ በኩል በክረምቱ ወራት በርበሬ፣ ጥቁር አዝሙድ፣ ቆንዶ በርበሬ፣ የስጋ መጥበሻና ኮረሪማ የመሳሰሉ የቅመማ ቅመም ዓይነቶች በስፋት እንደሚከተሉ ተናግረዋል። አርሶ አደሩ በተለይም ከበርበሬ፤ ከኮረሪማና ሌሎችም ተጠቃሚ እየሆነ ስለመጣ በልማት ስራው ላይ በከፍተኛ ፍላጎትና ተነሳሽነት እየተሳተፈ መሆኑንም ተናግረዋል። በ2017/18 የምርት ዘመን የተለያዩ የቅመማ ቅመም ዓይነቶችን በ600ሺ ሄክታር መሬት ላይ ለማልማት ታቅዶ የመሬት ዝግጅት ስራው መጠናቀቁን አመልክተዋል።
የድሬዳዋን ልማትና ኢንቨስትመንት ለማጠናከር ያለመ የዳያስፖራ ሳምንት ሊካሄድ ነው
Jun 13, 2025 55
ድሬዳዋ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ የድሬዳዋን ልማትና ኢንቨስትመንት ለማጠናከር ያለመ የዳያስፖራ ሳምንት ሊካሄድ መሆኑን የአስተዳደሩ ከንቲባ ጽህፈት ቤት ገለጸ። የከንቲባው ፅህፈት ቤት እና የካቢኔ ጉዳዮች ኃላፊ ገበየሁ ጥላሁን በሰጡት መግለጫ፤ በመላው አለም የሚገኙ የድሬዳዋ ተወላጆችና ወዳጆች የሚሳተፉበት አራተኛው አለም አቀፍ ሳምንት ለማክበር ዝግጅት ተጠናቋል። ከመጪው ሐምሌ 21/2017 ጀምሮ ለአንድ ሳምንት "ድሬ ናፍቆት ለድሬ ብልፅግና" በሚል መሪ ሀሳብ በሚከበረው በአል ላይ ከመላው አለም የሚመጡ የድሬዳዋ ተወላጆችና ወዳጆች በለውጥ ጉዞ ላይ ይመክራሉ ብለዋል። ባለፉት ሶስት አመታት የድሬዳዋ ተወላጆችና ወዳጆች የህዝቡን ማህበራዊ ችግሮች ከማቃለል፤ የወል ትርክትን በመገንባት ረገድ ጉልህ ድርሻ ማበርከታቸውን አንስተዋል። የዘንድሮውም ጅምር ስራዎችን በማጠናከር የድሬዳዋን የብልጽግና ጉዞ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሻገር የድርሻቸውን የሚወጡበት ነው ብለዋል። በድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ፅህፈት ቤት የዳያስፖራ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ዳይሬክተር ቢንያም ግርማ በበኩላቸው ቀደም ሲል የድሬዳዋ ተወላጆችና ወዳጆች ከ100 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የኩላሊት ዕጥበት ህክምና ማዕከል መገንባታቸውን ገልጸዋል። በተጨማሪም የትምህርት ቤት ምገባ እና የማዕድ ማጋራት ላይ መሳተፋቸውን አስረድተዋል። በኢንቨስትመንት ዘርፉም በስራ ዕድል ፈጠራና የዕውቀትና የቴክኖሎጂ ሽግግር ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል። ወደ ድሬዳዋ የሚመጡ ዳያስፖራዎችና ወዳጆች ከአስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በሀገራቸው የለውጥ ጉዞ ላይ እንደሚመክሩም ይጠበቃል ብለዋል። በተጨማሪም በኢንቨስትመንት አማራጮች፣ የቱሪዝም ሃብቶች ልማት ላይ እንደሚመክሩም ጠቁመዋል። እንዲሁም አስተዳደሩ ለዳያስፖራው ማህበረሰብ ባዘጋጀው መሬት ላይ የመኖሪያ ቤት ግንባታ እንደሚጀምሩም ገልጸዋል።
በክልሉ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ በሚደረገው ጥረት የታማኝ ግብር ከፋዮች ድርሻ ጉልህ ነው - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Jun 13, 2025 51
ሀዋሳ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ በሚደረገው ጥረት የታማኝ ግብር ከፋዮች ድርሻ ጉልህ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። በክልሉ "ታማኝ ግብር ከፋይ ብርቱ የልማት አርበኛ ነው" በሚል መሪ ሃሳብ ለግንባር ቀደም ግብር ከፋዮች የተዘጋጀ የእውቅናና ሽልማት መርሃ ግብር ተካሂዷል። ርዕሰ መስተዳድሩ በወቅቱ እንደተናገሩት በክልሉ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ በሚደረገው ጥረት የታማኝ ግብር ከፋዮች ሚና ጉልህ ነው። ባለፉት አምስት ዓመታት በተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መሰረተ ልማቶች ክልሉ በሚያመነጨው ገቢ የሚሰሩ በርካታ መሆናቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም ግብር ከፋዩ በክልሉ ልማትና እድገት ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ እንዲያጠናክርም አሳስበዋል። የክልሉ መንግስትም ለህዝቡና ለግብር ከፋዩ የተቀላጠፈ አገልግሎት በመስጠት የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ በትኩረት እንደሚሰራ ጠቅሰው የንግዱ ማህበረሰብ የሚያጋጥመውን ተግዳሮት የሚቀርፍ አሰራር መዘርጋቱን ተናግረዋል። የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ደምሴ እሳቱ በበኩላቸው የክልሉን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ የገቢ አቅምን የማሳደግና ገቢን በአግባቡ የመሰብሰብ ስራ በትኩረት እየተከናወነ ነው ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም 15 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ እቅድ ተይዞ እየተሰራ መሆኑን ገልጸው በ11 ወራት ውስጥ ከ12 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን ተናግረዋል። በቀሪ ወራትም የተያዘውን እቅድ በማሳካት በክልሉ ልማትና እድገት ላይ ጉልህ ሚና ለመጫወት በቅንጅት እየተሰራ ነው ብለዋል። እውቅናና ሽልማት የተሰጣቸው ታማኝ ግብር ከፋዮችም በ2016 በጀት ዓመት የሚጠበቅባቸውን ግብር በመክፈል የዜግነት ግዴታቸውን የተወጡ የሀገር ባለውለታ መሆናቸውን ገልጸዋል። እውቅናና ሽልማት ከተሰጣቸው ግብር ከፋዮች መካከል አቶ አብርሃም ኮባቶ ግብር መክፈል ለሀገር ልማትና የሚፈለገውን ብልጽግና ለማረጋገጥ የማይናቅ ድርሻ እንዳለው ተናግረዋል። የተሰጣቸው እውቅናም የበለጠ እንዲሰሩ ከፍተኛ አቅም እንደሚሰጣቸው በመግለጽ። ድርጅታቸው በተቋቋመ በአንድ ዓመት ውስጥ የሚጠበቅበትን ግብር በመክፈሉ እውቅና ማግኘቱን የገለጹት ደግሞ የሲዳማ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ኤሊያስ ቲሮ ናቸው። በቀጣይ የበለጠ በመስራት በሀገር ልማትና እድገት ላይ የበኩላቸውን እንደሚወጡም ገልጸዋል። ዛሬ እውቅናና ሽልማት የተሰጣቸው ግብር ከፋዮች ሁለት የልማት ድርጅቶችን ጨምሮ በቁጥር 55 ሲሆኑ ከ2 እስከ 57 ሚሊዮን ብር በላይ ግብርን በታማኝነት የከፈሉ መሆናቸውም ታውቋል። ለታማኝ ግብር ከፋዮቹም የሰርተፊኬት፣ የሜዳሊያና የዋንጫ እንዲሁም የተለያየ ሽልማትና እውቅና ተሰጥቷቸዋል።
ኢትዮጵያ ሰውሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን በመቋቋም የዘላቂ ልማት ግቦችን ለማሳካት ውጤታማ ሥራ አከናውናለች
Jun 13, 2025 62
አዲስ አበባ፤ሰኔ 6/2017 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ሰውሰራሽና ተፈጥሯዊ አደጋዎችን በመቋቋም የ2030 ዘላቂ የልማት ግቦችን የሚያሳኩ ውጤታማ ተግባራትን ማከናወኗን የ3ኛው ሀገር አቀፍ የዘላቂ ልማት ግቦች የፈቃደኝነት ግምገማ ሪፖርት አዘጋጅና የኢኮኖሚ አማካሪው ዳዊት አየለ ገለጹ። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ያጸደቀው የ2030 ዘላቂ የልማት አጀንዳ 17 ግቦችን ያካተተ ሲሆን፥ ከ2016 ጀምሮ ኢትዮጵያን ጨምሮ አባል ሀገራት በፈቃደኝነት ግቦችን ለማሳካት በትግበራ ላይ ይገኛሉ። 3ተኛው ሀገር አቀፍ የዘላቂ ልማት ግቦች ትግበራ የፈቃደኝነት ግምገማ ሪፖርትን የተመለከተ የምክክር መድረክ ሰኔ 2/2017 ዓ.ም መካሄዱ ይታወቃል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በወቅቱ ባስተላለፉት መልዕክት፥ ኢትዮጵያ የዘላቂ ልማት ግቦችን ከሀገራዊ የልማት ዕቅዶቿ ጋር በማስተሳሰር በከፍተኛ ኃላፊነት እየተገበረች እንደሆነ ተናግረዋል። በብዙ ፈተናዎች ውስጥ ሆና በርካታ የልማት ስራዎችን በማከናወን በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና በአካባቢ ጥበቃ ውጤት እያስመዘገበችና ዜጎቿን ተጠቃሚ እያደረገች ነው ብለዋል። በ3ኛው ሀገር አቀፍ የዘላቂ ልማት ግቦች የፈቃደኝነት ግምገማ ሪፖርት ዝግጅት የተሳተፉት የኢኮኖሚ አማካሪው ዳዊት አየለ፥ ኢትዮጵያ ሪፖርቱን ማዘጋጀቷ ስኬቶችንና ቀሪ ስራዎችን በመለየት ግቦችን ለማሳካት እንድትተጋ የሚያደርግ ነው ብለዋል። የግምገማ ሪፖርቱ እስከ ፈረንጆቹ 2030 ድረስ ባሉት አምስት ዓመታት ትኩረት የሚደረግባቸውን ጉዳዮች በመለየት ግቡን ሙሉ ለሙሉ ለማሳካት ትልቅ መነሻ እንደሚሆን አመልክተዋል፡፡ በሀገሪቱ የተከናወኑ የዘላቂ ልማት ግቦችን የገመገመ መሆኑን ጠቅሰው፥ ኢትዮጵያ በብዙ መልኩ ትልልቅ ስኬት ማስመዝገቧን ገልጸዋል። በተለይ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እንዲሁም ዘላቂ ልማትን የማረጋገጥ ተግባር ላይ የተሰሩ ስራዎች ከፍተኛ ውጤት እንደተመዘገበባቸው ጠቁመዋል፡፡ ማህበራዊ አገልግሎትን ከማስፋፋት አንጻር ጤና፣ ትምህርት፣ ውሃ፣ ኤሌክትሪክና ሌሎች ማህበራዊ ልማትን ለሁሉም ህብረተሰብ ለማቅረብ በተከናወኑ ተግባራት ከፍተኛ ዕድገት መምጣቱን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ለግቦች መሳካት አስፈላጊ የሆኑ የፖሊሲ ማዕቀፎችን በመተግበር ስኬታማ መሆኗንም ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት ካጋጠሙ በርካታ ሰው ሰራሽ እና የተፈጥሮ አደጋዎች አንጻር ከ60 በመቶ በላይ ግቦችን በስኬት እየፈጸመች መሆኗ የሚደነቅ ነው ብለዋል። እስካሁን የተመዘገቡ ውጤቶች በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት የዘላቂ ልማት ግቦቹ እንደሚሳኩ አመላካች መሆናቸውን አንስተው፥ በትኩረት መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ በተለይ የልጆች ጤና፣ ፍትሐዊ የማህበራዊ አገልግሎት ተደራሽነትን ለማጠናከር፣የሴቶችና የወጣቶችን እኩል ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ተጨማሪ እርምጃዎችን መውሰድና ኢንቨስትመንትን ፈሰስ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል፡፡ ለዚህም የባለድርሻ አካላትን፣የህብረተሰቡንና የግሉን ዘርፍ በማሳተፍ ተጨማሪ ሀብት ማሰባሰብ እንደሚገባ ጠቁመዋል። ይህን ማድረግ ከተቻለ ኢትዮጵያ ሁሉንም ግቦች በማሳካት በዓለም ላይ ውጤታማ ከሆኑ ሀገራት ተርታ መሰለፍ ትችላለች ብለዋል።
የመኖሪያ ቤት ችግርን ለማቃለል በተለያዩ አማራጮች የሚከናወኑ የቤት ግንባታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jun 13, 2025 65
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል የሚያግዙ የቤት ግንባታዎች በተለያዩ አማራጮች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባዋ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ፣ ጀርመን አደባባይ አካባቢ በመንግስት በጀት በመገንባት ላይ የሚገኙ የመኖሪያ ቤቶች የደረሱበትን ደረጃ ተመልክተዋል። የቤት ፍላጐት በመንግስት ብቻ ሊመለስ የሚችል ባለመሆኑ በግንባታ ስራ ላይ የተሰማሩ የግል አልሚዎች ግንባታዎቻቸውን ባጠረ ጊዜና በጥራት እንዲያጠናቅቁም ከንቲባዋ ጥሪያቸውን አቅርበዋል። የከተማ አስረተዳደሩም ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት አልሚዎች ግንባታዎቻቸውን በተያዘላቸው ጊዜ እንዲያጠናቅቁ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የመኖሪያ ቤት ችግርን ለማቃለል በተሰጠው ልዩ ትኩረት መሰረት በመንግስት፣ በመንግስትና በግሉ ዘርፍ እንዲሁም በግሉ ዘርፍ የግንባታ ፕሮጀክቶች እንዲፋጠኑ እየተደረገ እንደሚገኝ የከንቲባ ጽሕፈት ቤት ፕሬስ ሴክሬታሪያት ኃላፊ ሚኤሳ ኤለማ(ዶ/ር) ለኢዜአ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በመንግስት እየተከናወኑ ያሉ የቤት ግንባታ ፕሮጀክቶች እየተፋጠኑ እንደሚገኙ ገልጸው በተመሳሳይ መንግስት ከግሉ ዘርፍ ጋር እያከናወናቸው ያሉት ግንባታዎችም በመልካም ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በግሉ ዘርፍ እየተከናወኑ ላሉት የመኖሪያ ቤት ግንባታ ፕሮጀክቶችም መንግስት ከመሬት አቅርቦት ጀምሮ አስፈላጊ ጉዳዮችን በማሟላት እያገዘ በመሆኑ በተሻለ ደረጃ የሚንቀሳቀሱ እንዳሉ ጠቁመዋል። ኃላፊው አያይዘውም መሬት አጥረው ይዘው ወደ ተጨባጭ ስራ ያልገቡ የግሉ ዘርፍ የቤት አልሚዎች በፍጥነትና በጥራት ወደ ግንባታ እንዲገቡና የህዝቡን የቤት ፍላጎት እንዲያሟሉ ጥሪ አቅርበዋል።
በክልሉ ልማትና እድገትን ለማፋጠን አመራሩ ሚናውን በበለጠ ሊወጣ ይገባል-ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Jun 13, 2025 54
ባህር ዳር፤ሰኔ 6/2017 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ልማትና እድገትን ለማፋጠን በሚደረገው ጥረት አመራሩ ሚናውን በበለጠ ሊወጣ እንደሚገባ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ አስገነዘቡ። "አርቆ ማየት አርቆ መስራት" በሚል መሪ ሃሳብ የአማራ ክልል አሻጋሪ ዕድገትና የልማት ዕቅድ ዙሪያ ለክልሉ ከፍተኛ አመራሮች የተዘጋጀው የስልጠና መድረክ ዛሬ በባህር ዳር ተጀምሯል። ርዕሰ መስተዳደር አቶ አረጋ ከበደ በማስጀመሪያ ስነ-ስርአቱ ላይ እንደገለፁት፥በክልሉ ከድህነት ለመላቀቅ የሚያስችል የ25 አመት የፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቷል። ከፍኖተ ካርታው የተቀዳና ከ2018 በጀት ዓመት ጀምሮ የሚተገበር የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ መዘጋጀቱንም ተናግረዋል። እቅዱን በማሳካት የክልሉን ልማትና ዕድገት ለማፋጠን በሚደረገው ጥረት አመራሩ ሚናውን በበለጠ ሊወጣ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ ደመቀ ቦሩ (ዶ/ር) በበኩላቸው፥በክልሉ በየጊዜው የሚከሰቱ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ ችግሮች ክልሉ ባለው የመልማት ፀጋ ልክ ወደፊት እንዳይራመድ አድርገውታል ብልዋል ። ከችግሩ በዘላቂነት ለመላቀቅ የሚያስችል እቅድ መዘጋጀቱን ጠቅሰዋል። አመራሩ ስልጠናውን በትኩረት በመከታተል አሻጋሪ የልማት ዕቅዱ እንዲሳካ የላቀ ሚናውን እንዲወጣ አሳስበዋል። ዛሬ የተጀመረው የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና እስከ ሰኔ 13 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚቆይ የወጣው መርሃ ግብር አመላክቷል።
በሲዳማ ክልል ለግንባር ቀደም ግብር ከፋዮች እውቅናና ሽልማት እየተሰጠ ነው
Jun 13, 2025 55
ሀዋሳ፤ሰኔ 6/2017 (ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል ለግንባር ቀደም ግብር ከፋዮች የተዘጋጀ የእውቅናና ሽልማት መርሃ ግብር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ በተገኙበት እየተካሄደ ነው። የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን ያዘጋጀው መርሃ ግብር"ታማኝ ግብር ከፋይ ብርቱ የልማት አርበኛ ነው" በሚል መሪ ሀሳብ ነው እየተካሄደ የሚገኘው። ዛሬ እውቅናና ሽልማት የሚሰጣቸው ግብር ከፋዮች የሁለት የመንግስት የልማት ድርጅቶችን ጨምሮ በቁጥር 55 ሲሆኑ ከ2 እስከ 57 ሚሊየን ብር በላይ ግብር በታማኝነት የከፈሉ መሆናቸው ታውቋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉን ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች፤ ባለሃብቶችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በክልሉ ውጤታማ የመንግስት የፋይናንስ አስተዳደር ስርዓት ተግባራዊ በማድረግ የልማት ስራዎችን ለማፋጠን ትኩረት ተደርጓል-ርዕሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድ
Jun 13, 2025 49
ጋምቤላ፤ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦በጋምቤላ ክልል ውጤታማ የመንግስት የፋይናንስ አስተዳደር ስርዓት ተግባራዊ በማድረግ የልማት ስራዎችን ለማፋጠን ትኩረት መደረጉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ አለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። ክልል አቀፍ የፋይናንስ እና የገቢ ዘርፍ የምክክር መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ መካሄድ ጀምሯል። ርዕሰ መስተዳድሯ በምክክር መድረኩ ላይ እንዳሉት፥በክልሉ እየተከናወኑ የሚገኙ ማህበራዊ፣ኢኮኖሚያዊና ሌሎች መሠረተ ልማቶችን እውን ለማድረግ የተጠናከረ የፋይናንስ አቅም መገንባት ያስፈልጋል። ውጤታማ የመንግስት የፋይናንስ አስተዳደር ስርዓት ተግባራዊ ከማድረግ አኳያም የመንግስት የወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ማሻሻያ ሪፎርም በክልሉ ሲተገበር መቆየቱን አውስተዋል። በዚሁ መሰረት በበጀት አመቱ በክልሉ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን ስኬታማ ለማድረግም በትኩረት ሲሰራ መቆየቱን ገልፀዋል። በተለይም ክልሉ የሚሰበስበው ገቢ ድህነትን በመቀንስና ልማትን በሚያፋጥኑ የልማት ስራዎች ላይ ለማዋል የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ እንደነበሩ ተናግረዋል። በዚህም የክልሉ የድጎማ በጀትም ሆነ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱ እድገት እያሳየ መምጣቱ ለተመዘገቡት ውጤቶች አንዱ ማሳያ መሆኑንም ተናግረዋል። ይሁን እንጂ የመንግስትን ውስን በጀት በአግባቡ ጥቅም ላይ ከማዋልና ገቢን በአግባቡ ሰብስቦ ከመጠቀም አንፃር ውስንነቶች መኖራቸውን አንስተዋል። የዛሬው የምክክር መድረክ አላማም በፋይናንስ አስተዳደር፣አጠቃቀምና በገቢ አሰባሰብ ዙሪያ የሚስተዋሉ ዉስንነቶችን ለመፍታት ታሳቢ ያደረገ መሆኑን አብራርተዋል። የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ኡማን ኡጁሉ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት፥ ከተለያዩ የሀብት ምንጮች የሚገኘውን በጀት ቅድሚያ ለሚሰጣቸው የልማት ስራዎች ላይ ለማዋል ጥረት እየተደረገ ነው። የክልሉን የፋይናንስ ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል ከክልል ጀምሮ እስከ ወረዳ ድረስ ያለውን ቅንጅታዊ አሰራር ለማጠናከር እየተሰራ እንደሚገኝ ገልፀዋል። የምክክር መድረኩ በፋይናንስና በገቢ ዘርፍ የተደረጉ ማሻሻያዎች አተገባበርን በመገምገም በቀጣይ የተሻለ አፈፃፀም ለማስመዝገብ ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል። በምክክር መድረኩ ላይ የክልል፣የዞንና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የዘርፉ ከፍተኛ ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ ናቸዉ።
ኢትዮጵያ ወደ ቻይና የምትልካቸውን ምርቶች በአይነትና በመጠን ለማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ ነው-አምባሳደር ተፈራ ደርበው
Jun 12, 2025 166
አዲስ አበባ፤ሰኔ 5/2017 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ወደ ቻይና የምትልካቸውን ምርቶች በአይነትም በመጠን ለማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር ተፈራ ደርበው ገለጹ። አራተኛው የቻይና አፍሪካ የኢኮኖሚና ንግድ ኤክስፖ በቻይና ቻንግሻ ከተማ ዛሬ ተከፍቷል። ከኤክስፖው ጎን ለጎንም የኢትዮጵያን የአኩሪ አተር ተረፈ ምርት በቻይና ለማቅረብ የሚያስችል ስምምነት መፈረሙን የኢዜአ ሪፖርተር ከስፍራው ዘግቧል። ስምምነቱን በቻይና የኢትዮጵያ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ተፈራ ደርበውና የቻይና የጉምሩክ አጠቃላይ አስተዳደር ምክትል ሚኒስትር ዋንግ ልንግጁን ተፈራርመውታል። አምባሳደሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ስምምነቱ ለኢትዮጵያ አዲስ የገበያ እድል ከማስገኘቱ በተጨማሪ ወደ ቻይና የሚላኩ ምርቶችን መጠን ከፍ የሚያደርግ ነው። ስምምነቱ ባለፉት ስድስት ወራት በኢትዮጵያ የግብርና ባለስልጣንና በቻይና ጉምሩክ ባለስልጣን በጋራ ሲዘጋጅ መቆየቱን አንስተዋል። ስምምነቱ ከሀገሪቱ ጋር ያለውን የንግድ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚረዳ ገልጸው፤ኢትዮጵያ ወደ ቻይና የምትልካቸውን ምርቶች በአይነትም በመጠንም ለማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በተመሳሳይም አምባሳደር ተፈራ 'ከቻንግሻ ሳተርንበርድ ኮፊ ኤልቲዲ' (Changsha Saturnbird Coffee Co., LTD.) መስራች እና ሊቀመንበር ሚስተር ው ጁን ጋር የኢትዮጵያ ቡናን እሴት ጨምሮ ለቻይና ገበያ ለማቅረብ እንዲችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ኩባንያው የኢትዮጵያ ቡናን በብዛት በመግዛት ለሌሎች የቻይና ቡና ኩባንያዎች ለማከፋፈል፣ ቆልቶ ለማዘጋጀት፣ለመፍጨት እና የቡና ምርቶች ለማዘጋጀት እንደግብዓት የሚጠቀም መሆኑ ተገልጿል።