ኢኮኖሚ
የሚሰሩ እጆችን ከስራ እያገናኘን፣ የሚፈጥር አዕምሮን ወደ ተግባር እያስገባን የተሻለ የስራ ዕድል ለመፍጠር እየሰራን ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 27, 2024 41
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2016(ኢዜአ)፦ የሚሰሩ እጆችን ከስራ እያገናኘን፣ የሚፈጥር አዕምሮን ወደ ተግባር እያስገባን የተሻለ የስራ ዕድል ለመፍጠር በመስራት ላይ እንገኛለን ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከአምራች ኢንዱስትሪዎች ጋር ውይይት በማድርግ ወደ ላቀ ደረጃ የተሸጋገሩ አምራቾችን መሸለማቸውን ገልጸዋል።   ከንቲባዋ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት “ኢትዮጵያ-ታምርት፤ እኛም እንሸምት” በሚል መሪ ሃሰብ በተቀናጀና ቀጣይነት ባለው የድጋፍ ማዕቀፍ የአምራች ኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት ለማሳደግ በተዘጋጀ የንቅናቄ ማጠቃለያ መድረክ ላይ መገኘታቸውን ጠቁመዋል። ከንቲባ አዳነች የሚሰሩ እጆችን ከስራ እያገናኘን፣ የሚፈጥር አዕምሮን ወደ ተግባር እያስገባን ከዝቅተኛ እስከ ከፍተኛ ያሉ አምራች ኢንዱስትሪዎች ያነሷቸውን ቅሬታዎች በመፍታት የተሻለ የስራ ዕድል ለመፍጠር በመስራት ላይ እንገኛለንም ብለዋል።   ባለው የድጋፍ ማዕቀፍ በፍትሃዊነት እያስተናገድን፣ የሚቀሩትን በጋራ ጥረት እያሟላን የኢንዱስትሪ ዘርፉን የማምረት አቅም እያሻሻልን እና የሚነሱ ቅሬታዎችን በጋራ እየቀረፍን ለወጣቶቻችን በቂ የስራ እድል የሚፈጥር የኢንዱስትሪ ዘርፍ እንገነባለን ሲሉም ገልጸዋል በመልዕክታቸው።
በሲዳማ ክልል በበልግ እርሻ 112 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር ተሸፍኗል
Apr 27, 2024 50
ሀዋሳ፤ ሚያዚያ 19/2016 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በበልግ እርሻ 112 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር መሸፈኑን የክልሉ ግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። በሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ የተመራ ቡድን በተለያዩ ወረዳዎች በበልግ እርሻ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን እየተመለከተ ነው። በጉብኝቱ ላይ የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎን ጨምሮ ሌሎች የክልል፣ የዞንና ወረዳ የሥራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል። በቦርቻ ወረዳ ፍላሳ ቀበሌ በክላስተር የለማ የበቆሎ ማሳን በጎበኙበት ወቅትም ርዕሰ መስተዳድሩና ሌሎች የክልሉ አመራር አባላት የኩትኳቶ ስራ በማከናወን ላይ የሚገኙ አርሶ አደሮችን አበረታተዋል። የሲዳማ ክልል ግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ባንጉ በቀለ ለኢዜአ እንደገለጹት ጉብኝቱ የበልግ እርሻ ልማት ያለበትን ደረጃ ለመቃኘት ያለመ ነው። በክልሉ በበልግ እርሻ 112 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር መሸፈኑን ገልጸው፣ ከዚህ ውስጥ ከ68 ሺህ ሄክታር የሚበልጠው መሬት በዋና ዋና ሰብሎች መልማቱን ተናግረዋል። የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግም በ25ሺህ 284 ሄክታር መሬት ላይ በቆሎ በኩታ ገጠም መልማቱን አስረድተዋል። በክልሉ በአሁኑ ወቅት የተስተካከለ የበልግ ዝናብ ስርጭት መኖሩን የጠቀሱት አቶ ባንጉ፣ በዘር ከተሸፈነው መሬትም 14 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ይገኛል ተብሎ ይጠበቃል። የወረዳው አርሶ አደሮች በበኩላቸው በኩታ ገጠም ልማት ተመሳሳይ ሰብል ማልማታቸው የተሻለ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል። በተያዘው የበልግ እርሻም በኩታ ገጠም ያለሙት የበቆሎ ሰብል በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ጠቁመው፣ ከዚህም በሄክታር እስከ 60 ኩንታል ምርት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። የመስክ ምልከታው በቀጣይም በሎካ አባያ እና ብላቴ ዙሪያ ወረዳዎች እንደሚካሄድ ታውቋል።
በአማራ ክልል ከ12 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ የቡናና ፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ
Apr 27, 2024 48
ደሴ፤ ሚያዝያ 19/2016(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር የሚተከሉ ከ12 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ የቡናና ፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር ቡናና ፍራፍሬን ጨምሮ 1 ነጥብ 7 ቢሊዮን የተለያዩ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑንም ቢሮው ገልጿል። ቢሮው በአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር በክልሉ ለሚተከለው የቡናና ፍራፍሬ ችግኝ ቅደመ ዝግጅት የንቅናቄ መድረክ በኮምቦልቻ ከተማ ተካሂዷል። በዚህ ወቅት የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ቃልኪዳን ሽፈራው እንደገለጹት፣ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር በክልሉ የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲለሙ ብሎም የደን ሽፋንን ለማሳደግ እየረዳ ይገኛል። እንዲሁም አርሶ አደሩ ከቡናና ፍራፍሬ ልማት ተጨማሪ ገቢ በማግኘት የኢኮኖሚ አቅሙ እንዲጠናከር በማድረግ በኩል አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ለማጠናከር ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር የሚተከሉ 1 ነጥብ 7 ቢሊዮን የተለያዩ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን ገልጸዋል። ከሚተከሉት ችግኞች 18 ነጥብ 5 ሚሊዮን ቡናና ፍራፍሬ መሆናቸውን ያመለከቱት አቶ ቃልኪዳን፤ እስካሁንም ከ12 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ የቡናና ፍራፍሬ ችግኞች ተዘጋጅተዋል ብለዋል። የቡናና የፍሬፍሬ ችግኞቹ የተፈጥሮ ሀብት ልማት በተከናወነባቸው ተፋሰሶች እና በአርሶ አደሩ ማሳ እንደሚተከሉ ጠቁመው፣ ለዚህም ከ3ሺህ 700 ሄክታር በላይ መሬት መለየቱን አስተውቀዋል። በደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ የአትክልትና ፍራፍሬ መስኖ ውሃ አጠቃቀም ቡድን መሪ አቶ አሳልፍ አህመድ በበኩላቸው፣ በዞኑ በቡናና ፍራፍሬ ልማት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው። ባለፉት ዓመታት ከ6ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቋሚ ፍራፍሬ መልማቱን አውስተው፤ ከዚህ የሚገኘው ምርት ከአካባቢው ተርፎ ሌሎች አካባቢዎች ገበያ እየቀረበ ነው ብለዋል። በዞኑ ከ1 ሚሊዮን 500 ሺህ በላይ የቡናና የፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል የዝግጅት ሥራ እየተከናወነ መሆኑንም ነው ቡድን መሪው ያመለከቱት። የቡናና ፍራፍሬ ልማት በክላስተር ጭምር በመጀመሩ አርሶ አደሩ ተጠቃሚ እየሆነ ነው ያሉት ደግሞ በክልሉ የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ግብርና መምሪያ ተወካይ አቶ ቦጋለ መንግስቱ ናቸው። በዞኑ በቀጣዩ የክረምት ወቅት ለሚከናወነው የችግኝ ተከላ መርሀ-ግብር የተለያዩ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራሮች እንዲሁም ባለሙያዎች ተሳታፊ ሆነዋል።
በጋምቤላ ክልል ገቢን በማሳደግና በጀትን በአግባቡ በመጠቀም ለልማት ዕቅዶች ውጤታማነት ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ
Apr 27, 2024 55
ጋምቤላ፤ ሚያዝያ 19/2016 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል የገቢ አቅምን በማሳደግና በጀትን በአግባቡ በመጠቀም የልማት ዕቅዶችን ውጤታማ ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኡሞድ ኡጁሉ ገለጹ። ክልል አቀፍ የፋይናንስና የገቢ ዘርፍ የጋራ የምክክር መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ እየተካሄደ ነው። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት የክልሉን ህዝብ የልማት ጥያቄዎችን ለመመለስ ያለውን ውስን በጀት በአግባቡ በመጠቀምና የገቢ አቅምን ማሳደግ ያስፈልጋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት ያለውን በጀት ሁለንተናዊ ዕድገትን በሚያመጡ የልማት ዘርፎች ላይ ለማዋል በትኩረት ሲሰራ መቆየቱን አውስተዋል። የመንግስት የፋይናንስ አስተዳደርን ውጤታማ ለማድረግም የገቢ አሰባሰብ ስርዓት፣ የወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ማሻሻያዎች ሲተገበሩ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ኡሞድ፣ በዘርፉም አበረታች ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል።   ሆኖም በጀትን በአግባቡ ባለመጠቀምና ክልሉ የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ ያለመሰብሰብ ችግሮች በየዓመቱ ለበጀት ጉድለት ምክንያት መሆናቸውን አንስተዋል። በተጨማሪም ከአደረጃጀትና ከመዋቅር መስፋት ጋር ተያይዞ የሚደረግ የሰው ሃይል ቅጥርና ምደባ ለበጀት ጉድለት መንስኤ መሆናቸውን ነው ርዕሰ መስተዳድሩ የጠቀሱት። የበጀት አጠቃቀምንና የገቢ አሰባሰብ ስርዓቱን ይበልጥ በማዘመንና በማሻሻል የታለሙ የልማት ግቦችን እውን ለማድረግ በትኩረት ልንሰራ ይገባል ሲሉም አሳስበዋል።   የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡቦንግ ኡቶው በበኩላቸው በክልሉ በየዓመቱ የሚመደበውን በጀት ቅድሚያ ለሚሰጣቸው የልማት ዘርፎች በማዋል የህዝቡን መሰረታዊ የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ጥረት ሲደረግ መቆየቱን አስታውሰዋል። በክልሉ የሚሰበሰበው ገቢ በየዓመቱ እየተሻሻለ መምጣቱንም ተናግረዋል። ያለውን በጀት በአግባቡ ልማት ላይ በማዋል በኩል የሚታዩ ውስንነቶችን በማስተካከል የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። በመድረኩ ላይ ከክልል እስከ ወረዳ የሚገኙ የዘርፉ አመራር አባላትና ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ ናቸው።  
የኢትዮ-ጅቡቲ ምድር ባቡር ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ2 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ አገኘ
Apr 27, 2024 57
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2016(ኢዜአ)፡- የኢትዮ-ጅቡቲ ባቡር ትራንስፖርት አክሲዮን ማኅበር ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከተጓዦችና የጭነት አገልግሎት ከ2 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን አስታወቀ። የኢትዮ-ጅቡቲ ምድር ባቡር ትራንስፖርት አክሲዮን ማኅበር ዋና ሥራ አስፈጻሚ አብዲ ዘነበ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ማኅበሩ መንገደኞችንና ጭነትን የማጓጓዝ አገልግሎት እየሰጠ ነው ብለዋል። ማኅበሩም በየቀኑ ከ700 እስከ 1ሺህ ሰዎችን በማጓጓዝ የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነትን ለጠንካራ ቀጣናዊ የኢኮኖሚና ማኅበራዊ ትስስር ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ገልፀዋል። በሁለቱም ሀገራት የሰበታና ሆልሆልን ጨምሮ አዳዲስ የባቡር መዳረሻዎችን ወደ ሥራ በማስገባት የዜጎችን የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ መሠረተ-ልማት መገንባት እንደሚቻል ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል። የባቡሩ ትራንስፖርት አገልግሎት ሥራ በጀመረባቸው ባለፉት ስድስት ዓመታት ጊዜ በየዓመቱ ከ35 እስከ 41 በመቶ የሚደርስ እድገት እያስመዘገበ መሆኑን ጠቁመዋል። በዘጠኝ ወራት ጊዜ ውስጥ ከ155 ሺህ በላይ ተጓዦችን እና 1 ነጥብ 4 ሚሊየን ቶን የጭነት አገልግሎት በማጓጓዝ የዕቅዱን 98 በመቶ ማሳካት እንደተቻለ አስታውቀዋል። በበጀት ዓመቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሰጠው ተጓዞችንና ጭነት የማጓጓዝ አገልግሎት ከ2 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ ማግኘት እንደተቻለ ተናግረዋል። የኢትዮ-ጅቡቲ ምድር ባቡር ባለቤትነት የሁለቱ ሀገራት መሆኑን ያነሱት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ የባቡር ትራንስፖርት አገልግሎቱ ሲጀመርም ሀገራቱ የጋራ ተጠቃሚነት ዓላማ በማስቀመጥ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያም በኩል የተሳለጠ የወጪና ገቢ ምርት የሎጂስቲክስ አገልግሎት በመስጠት የኢንዱስትሪ ሽግግርን ለማሳለጥ ዓላማ አድርጎ የተገነባ መሠረተ-ልማት መሆኑን ገልፀዋል። በግብርና መስክ የቁም እንስሳት፣ የቡና እና የአፈር ማዳበሪያን ጨምሮ የማዕድንና ኢንዱስትሪ ወጪና ገቢ ምርት በማጓጓዝ ለኢኮኖሚ ዕድገት መሳለጥ ፈጣን አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ አንስተዋል። የኢትዮ-ጅቡቲ ምድር ባቡር ትራንስፖርት አክሲዮን ማኅበርን የማስተዳደር፣ የመጠገንና የመከታተል ሥራ በውጭ አገር ኮንትራክተር ሲከናወን መቆየቱን አንስተዋል። ከ13 እስከ 15 በመቶ የወጪና ገቢ ምርት የሚያጓጉዘውን ማኅበር እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2024 ጥር ወር ጀምሮ ኢትዮጵያ የማስተዳደር ኃላፊነት ወስዳ እየሰራች መሆኗን ገልፀዋል። በባቡር ትራንስፖርት ምቹ ምኅዳር በመፍጠርም በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ውስጥ የገቢና ወጪ ምርት የማጓጓዝ አቅም የበለጠ ለማሳደግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው ብለዋል። በአጠቃላይ ከ1ሺህ በላይ የተለያየ አገልግሎት የሚሰጡ ባቡሮች የኢትዮጵያን ወጪና ገቢ ምርት በማጓጓዝ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚያዊ እድገት እየደገፉ እንደሚገኝ ገልፀዋል። የኢትዮ-ጅቡቲ ምድር ባቡር ትራንስፖርት የሁለቱን አገራት ዜጎች በማገናኘት ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ፋይዳ እያበረከተ እንደሚገኝ አንስተዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ9 ወራት የሥራ አፈጻጸም እየተገመገመ ነው
Apr 27, 2024 68
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2016(ኢዜአ)፡- የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዘጠኝ ወራት የሥራ አፈጻጸም እየተገመገመ ነው፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ የበጀት ዓመቱን የዘጠኝ ወራት የስራ አፈጻጸማችንን እየገመገምን ነው ብለዋል፡፡   በግምገማ መድረኩ ላይ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ንግግር አድርገዋል፡፡ በንግግራቸውም ባለፉት ዘጠኝ ወራት የህዝባችንን የኑሮ ጫና ለማቅለል እና የተጀመሩ ትላልቅ ፕሮጀክቶቻችንን በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅ አዳጊና ተደማሪ የሆኑ አዳዲስ እይታዎችን ተግባራዊ በማድረግ፣ ውጤታማ የስራ ባህል በመከተል እንዲሁም የአመራር ቅንጅትን ይበልጥ በማጎልበት የተከተልነው መንገድ ውጤታማ ያደረገን ነበር ሲሉ ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም ክፍተቶቻችንን በመሙላት ለህዝባችን የገባነውን ቃል በተግባር ለማዋል የምንሰራ ይሆናል ማለታቸውን የከንቲባ ጽህፈት ቤት መረጃ አመላክቷል፡፡
በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የተመራ ልዑክ በአካባቢው የሚገኙ ልዩ ልዩ የልማት ስራዎችን ለመመልከት ኮምቦልቻ ገባ
Apr 27, 2024 61
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2016(ኢዜአ)፡- በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የተመራ የፌደራል መንግሥት እና የአማራ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ልዑክ በአካባቢው የሚገኙ ልዩ ልዩ የልማት ስራዎችን ለመመልከት ኮምቦልቻ ገብቷል፡፡ ልዑኩ ኮምቦልቻ ከተማ ሲደርስ በአማራ ክልል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እና በከተማው ነዋሪዎች አቀባበል ተደርጎለታል፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ በቆይታችን በአካባቢው የሚገኙ ልዩ ልዩ የልማት ስራዎችን የምንጎበኝ ይሆናል ብለዋል፡፡ የልዑካን ቡድኑ አባላት በኮምቦልቻ በሚኖራቸው ቆይታ በከተማዋ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ሥራዎችን እንደሚመለከቱ ይጠበቃል፡፡ በምክትል ጠቅላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የተመራው ልዑክ የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህን ጨምሮ ሌሎች የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችን ያካተተ ነው፡፡
ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት በተደረጉ የፋይናንስ እና ካፒታል ገበያ ዘርፎች ላይ በኔዘርላንድስ ለሚገኙ አምራች ኩባንያዎች ማብራሪያ ተሰጠ
Apr 27, 2024 56
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2016(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ በቅርቡ ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት በተደረጉ የፋይናንስ እና ካፒታል ገበያ ዘርፎች ላይ በኔዘርላንድስ ለሚገኙ አምራች ኩባንያዎች ማብራሪያ ተሰጠ፡፡ ማብራሪያውን የሰጡት የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ዳጋቶ ኩምቤ ናቸው፡፡ በአቶ ዳጋቶ ኩምቤ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ በኔዘርላንድስ አምስተርዳም “የአፍሪካ አረንጓዴ ኢንደስትሪያላይዜሽን - በአፍሪካ የተሰራ” በሚል መሪ ሀሳብ በብራሰልስ በተዘጋጀው ’AFRICA 20 Works! 24’ የኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ሁነት ላይ ተካፍሏል፡፡ የኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ሁነቱ በኢትዮጵያ ኤምባሲ እና በኔዘርላንድስ አፍሪካ የቢዝነስ ካውንስል አማካኝነት መዘጋጀቱን ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡   በሁነቱም በመንግስት ቅድሚያ ተሰጥቶ እየተሰራባቸው ባሉ የኢንቨስትመንት ዘርፎች እና አማራጮች ዙሪያ እንዲሁም በሁነቱ መሪ ቃል ላይ ያተኮረ ገለጻ ማድረጋቸውም ተጠቁሟል፡፡ ለውጭ ባለሀብቶች ክፍት በተደረጉ የፋይናንስ እና ካፒታል ገበያ ዘርፎች ላይ አቶ ዳጋቶ ኩምቤ ተጨማሪ ማብራሪያ መስጠታቸውም በመረጃው ተመላክቷል፡፡ በቤልጂየም የኢፌዲሪ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ሂሩት ዘመነ እና ምክትል ኮሚሽነር ዳጋቶ ኩምቤ ከተሳታፊዎች ለተነሱ አስተያየቶችና ጥያቄዎች ምላሽ እና ማብራሪያ መስጠታቸውም ተጠቁሟል፡፡ በሁነቱ ከተሳተፉ አምራች ኩባንያዎች እና ባለሀብቶች ጋር የአንድ ለአንድ ውይይት መደረጉም ተመላክቷል፡፡ ልዑኩ በኔዘርላንድስ በተለይም በአግሮ ሎጀስቲክስ ዘርፍ ላይ የተሰማሩ አምራች ድርጅቶችን መጎብኘቱም ተጠቁሟል፡፡
በክልሉ የኑሮ ውድነትና ሥራ አጥነትን ለመቀነስ በተደረገ ጥረት ውጤት ተመዝግቧል- ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Apr 26, 2024 77
አርባ ምንጭ ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ባለፉት ዘጠኝ ወራት የኑሮ ውድነትንና ሥራ አጥነትን ለመቀነስ በተደረገው ጥረት ውጤት መገኘቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ክልል አቀፍ የኑሮ ውድነት ማረጋጋትና የክህሎት-መር ሥራ ዕድል ፈጠራ ንቅናቄ መድረክ ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል።   ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን በመድረኩ ላይ እንደተናገሩት ባለፉት ዘጠኝ ወራት የኑሮ ውድነትና ሥራ አጥነትን ለመቀነስ በተደረጉ ጥረቶች አበረታች ውጤት ተመዝግቦበታል። የኑሮ ውድነትን ለመቀነስ ክልሉ ያለውን ሰፊ ፀጋና አቅም በማስተባበር እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ምርትና ምርታማነት በመጨመር፣የገበያ አማራጮችን በማስፋት እንዲሁም ህገ-ወጥ እንቅስቃሴዎችን በመቆጣጠር የህዝቡን ፍላጎትና አቅርቦት ለማጣጣም ጠንካራ ሥራ ተሠርቷል ብለዋል ርዕሰ መስተዳድሩ። በቀጣይ መሠረታዊ የግብርና ምርቶች በስፋትና በጥራት እንዲቀርቡ በማድረግና ህገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን በመቆጣጠር የኑሮ ውድነት ለመቀነስ እንደሚሠራም ገልጸዋል። በክልሉ ሥራ አጥነትን ለመቀነስ ሥራ አጦችን በመለየትና ደረጃ በደረጃ የሥራ ዕድል ለመፍጠር የተደረገው ጥረት ውጤት ማስገኘቱን አስታውቀዋል። በዚህም በመሠረታዊነት በግብርናና በቱሪዝም ዘርፎች ለማሰማራት የወጣቱን ክህሎትና ዕውቀት በማሳደግ በትኩረት እንደሚሠራ ርዕሰ መስተዳድሩ አመልክተዋል። የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ገሌቦ ጎልቶሞ በበኩላቸው የኑሮ ውድነት ችግር ለመቀነስ በተቀናጀና በተደራጀ መንገድ በመሰራቱ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል።   የግብርና ምርቶች በስፋት በማቅረብ፣ አርሶ አደሮች፣ አልሚ ባለሀብቶችንና ማህበራትን በማስተሳሰርና አማራጭ የገበያ ዕድሎችን በመፍጠር የዋጋ ንረቱ እንዲረግብ መደረጉን ገልጸዋል። በምርት እንቅስቃሴ ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደሩ የሚገኙ 40 ህገ-ወጥ ኬላዎችን በማስወገድ፣ 253 ህገ-ወጥ ደላሎችን ከሰብልና ከእንስሳት ግብይት ማስወጣት እንደተቻለ ሃላፊው አስታውቀዋል። በክልሉ 67 የሰንበት ገበያዎች አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉን የገለጹት አቶ ገሌቦ፣ በግብርና ዘርፍ የተሰማሩ ወጣቶች አትክልትና ፍራፍሬ በስፋት በማምረታቸው ገበያው መረጋጋት አሳይቷል ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመት በሥራ አጥነት ከተለዩ 250 ሺህ ዜጎች መካከል ለ112 ሺህ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ በለጠ ሙኒኤ ናቸው። ከነዚህም መካከል ከ21 ሺህ የሚልቁ ወጣቶች የውጭ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆናቸውንም አስታውቀዋል። በቀጣይ ወጣቱ በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ በተሰማሩበት የሥራ ዘርፍ ውጤታማ እንዲሆኑ ክህሎት መር ስልጠና በመስጠት ብቁ ዜጎችን ለማፍራት እንደሚሠራም አቶ በለጠ ገልጸዋል። የክልሉ ቴክኒክና ሙያ ትምህርት ስልጠና ቢሮ ሃላፊ አቶ አብዮት ደምሴ በበኩላቸው የሚፈጠረው የሥራ ዕድል በዕውቀትና ክህሎት ታግዞ ውጤታማ እንዲሆን ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። ቢሮው በዘርፉ የሚስተዋሉ የዕውቀትና የክህሎት ክፍተቶችን ለመሙላት ለሀገር ውስጥና ለውጭ ሥራ ስምሪት የሚበቁ ወጣቶችን በመፍጠር ሃላፊነቱን እንደሚወጣ ተናግረዋል። ለአንድ ቀን በተዘጋጀው መድረክ ላይ የክልሉና የዞኖች ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ሃላፊዎችና የዘርፉ ባለሙያዎች ተገኝተዋል።    
ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራዎችን በማጠናከር የዜጎችን ተጠቃሚነት ማጎልበት ይገባል
Apr 26, 2024 64
ጋምቤላ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራዎችን በማጠናከር የዜጎችን ተጠቃሚነት ማጎልበት እንደሚገባ የሥራና ክህሎት ሚንስትር ዴኤታ አቶ ሰለሞን ሶካ ገለፁ። በሚንስትር ዴኤታው የተመራ የፌዴራል የድጋፍና ክትትል ሱፐርቪዥን ቡድን በጋምቤላ ክልል በስራና ክህሎት ቢሮ እየተተገበሩ ባሉ የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራዎች ላይ ውይይት አካሂዷል።   የሥራና ክህሎት ሚንስትር ዴኤታ አቶ ሰለሞን ሶካ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፣ ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ሥራዎች እንዲጠናከሩ በመንግስት በኩል ትኩረት ተሰጥቷል። በተለይም ሥራ አጥነትና የኑሮ ውድነት ፈተና መሆናቸውን ጠቁመው፣ ችግሮቹን ደረጃ በደረጃ ለመፍታት ለክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት መስጠት እንደሚገባ አመላክተዋል። ለሥራ አጥ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ፋይዳው የላቀ በመሆኑ ለዘርፉ መጠናከር በቅንጅት ልንሰራ ይገባል ብለዋል። ሚኒስቴሩ እንደ ሀገር 3 ነጥብ 9 ሚሊዮን ለሚሆን ሥራ አጥ ዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር ግብ ይዞ እየሰራ መሆኑንም ሚንስትር ዴኤታው አስረድተዋል። እንደ አቶ ሰለሞን ገለጻ በጋምቤላ ክልል ያሉ የተፈጥሮ ፀጋዎችን ለሀገርና ለክልሉ እድገት የሚያውል ክህሎት ያለው የሰው ሃይል ማፍራት ላይ የተጀመሩ ጥረት መጠናከር ይገባቸዋል። የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኡሞድ ኡጁሉ በዚሁ ጊዜ በስራ ዕድል ፈጠራ የተጀመሩ አበረታች ስራዎች ቢኖሩም፤ በቀጣይ ለማጠናከር እንደሚሰራ ገልጸዋል።   ለእዚህም በክልሉ ያሉትን የመሬት፣ የውሃ፣ የማዕድንና ሌሎች የተፈጥሮ ሃብቶች ላይ ተሰማርተው ራሳቸውንና አካባቢያቸውን የሚለውጡ ሥራ አጥ ወጣቶችን አሰልጥኖ ለማሰማራት የተጀመረው ሥራ እንደሚጠናከር ነው ያስታወቁት። የቡድኑ አባላት በጋምቤላ ክልል በሚኖራቸው የአንድ ሳምንት ቆይታ በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በክህሎት መር ልማት፣ በተቋማት ግንባታና በሠራተኛና አሰሪ ሰላማዊ ግንኙነት ላይ ምልከታ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በምልከታው ማጠቃለያም ቡድኑ ግብረ መልስ በመስጠት ለቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ እንደሚያስቀምጥ ታውቋል።
ፒያሳን የቱሪስት መስህብ የሚያደርግ የልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑ ተገለጸ
Apr 26, 2024 59
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ ፒያሳን በመሰረተ ልማት በማስተሳሰር ትልቅ የቱሪስት መስህብ ለማድረግ የሚያስችል የልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 3ኛ አመት የስራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ጉባኤውን ዛሬ አካሂዷል።   ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአዲስ አበባ ከተማ እየተካሄደ ያለውን የኮሪደር ልማትና የአድዋ ዙሪያ መልሶ ማልማት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። በዚሁ ወቅት አራት ኪሎና ፒያሳ በርካታ ቅርሶች የሚገኙባቸው አካባቢዎች መሆናቸውን ያነሱት ከንቲባዋ የአካባቢውን የቱሪዝም መስህብ ለመጨመር በኮሪደር ልማቱ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። በዚህም በኮሪደር ልማቱ በመታገዝ አካባቢዎቹን በመሰረተ ልማት፣ በመጋቢና ሰፋፊ መንገዶች ለማገናኘት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። አካባቢው የአድዋ ድል መታሰቢያ፣ የአጼ ምኒሊክና አቡነ ጴጥሮስ ሃውልት፣ማዘጋጃ ቤትና ሌሎች ጥንታዊና ታሪካዊ ቦታዎች የሚገኙበት በመሆኑ ሃብቱን መጠቀም በሚያስችል መልኩ እየተሰራ ነው ብለዋል። በተጨማሪም በከተማዋ የመጀመሪያው ሆቴል፣ ቲያትርና ሲኒማ ቤቶች እንዲሁም ሌሎች ታሪካዊ ቅርሶች የሚገኙበት በመሆኑ ለቱሪስቶች አመቺ በሚሆን መልኩ ለማስተሳሰር እየለማ መሆኑን ገልጸዋል። ለአገር ውስጥም ይሁን ለውጪ ጎብኝዎች የአድዋ ድል መታሰቢያን ጨምሮ ሌሎች የቱሪስት ግብአቶችን በሚያሰፋ መልኩ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። የአደጉ አገሮች ታሪካዊ ቅርሶቻቸውን በማልማትና በመሰረተ ልማት በማስተሳሰር እየተጠቀሙበት መሆኑን በመጥቀስ በአዲስ አበባም በዚህ መልኩ እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ከንቲባዋ በከተማዋ እየተካሄደ ባለው ልማት "ለኢትዮጵያ ትልልቅ ቅርስ እየጨመርን እንጂ ቅርስ እያጠፋን አይደለም" ብለዋል። በመሆኑም ለቅርስ ጥበቃ፣ እድሳትና እንክብካቤ ማድረግ ለቱሪስት መስህብነትና ለታሪክ መጉላት አስተዋጽኦ ያደርጋል ነው ያሉት። የኮሪደር ልማትን ከማገናኘት በተጨማሪ ለህዝብ መዝናኛ፣ ለአውቶቡስና ታክሲ ተርሚናል የሚውል 60 ሔክታር መሬት መጽዳቱን ጠቁመዋል።    
በከተማዋ የኮሪደር ልማት ለግል ይዞታ ተነሺዎች ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ካሳ ተከፍሏል
Apr 26, 2024 72
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ኮሪደር ልማት ለግል ይዞታ ተነሺዎች ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ካሳ መከፈሉን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናገሩ። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 3ኛ አመት የስራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ጉባኤውን ዛሬ አኳሂዷል።   ከንቲባ አዳነች አቤቤ በአዲስ አበባ ከተማ እየተካሄደ ያለውን የኮሪደር ልማትና የአድዋ ዙሪያ መልሶ ማልማት እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። ከንቲባዋ በሪፖርታቸው የኮሪደር ልማት ለከተማዋና ለነዋሪዎቿ ያለውን ፋይዳ፣ የትግበራ ሂደት፣ የተገኙ ውጤቶችን እንዲሁም ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎችን አቅርበዋል። በትግበራ ሂደቱ መኖሪያ ቤት ማስተላለፍ፣ ለንግድ ቤቶችና ለግል ባለይዞታዎች ምትክ መሬትና የካሳ ክፍያዎችን በመፈጸም የተከናወኑ ተግባራትን ዝርዝረዋል። በዚህም ለ307 የግል ይዞታ ተነሺዎች 2 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር የካሳ ክፍያ ለመፈጸም መወሰኑንና እስካሁን 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ካሳ መከፈሉን ገልጸዋል። በተመሳሳይ ለ417 የቀበሌ ንግድ ቤቶች እና ለ393 የፌደራል ኪራይ ቤቶች ባለይዞታዎች 30 ሄክታር ምትክ መሬት ተዘጋጅቶ እየተስተናገዱ መሆኑን አመላክተዋል። የከተማ ፕላን መስፈርቶችን መሰረት በማድረግ የፍሳሽ ማስወገጃ፣ የመብራት፣ ቴሌኮም፣ የደህንነት መጠበቂያ ካሜራ በመሬት ውስጥ እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም ከተማዋን ከድንገተኛና ሰው ሰራሽ የተፈጥሮ አደጋዎች ለመታደግ ያግዛል ብለዋል። እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት ማህበራዊ ችግርን በመፍታት፣ የትራፊክ ፍሰትን በማሳለጥ፣ ዘመናዊ ከተማን እውን ከማድረግ አንጻር ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው በቀረበው ሪፖርት ላይ አስተያየት የሰጡ የምክር ቤት አባላት አንስተዋል። በትግበራው የልማት ተነሺዎች ተገቢውን ቦታና ካሳ እንዲያገኙና ቅርሶች እንዲጠበቁ ክትትል ሲያደርጉ መቆየታቸውን አንስተዋል። የስራ ትስስር፣ ለተነሺዎች ያልተሟሉ መሰረተ ልማቶችን ማሟላት፣ የታጠሩ ቦታዎች ፈጥነው ወደ ስራ እንዲገቡ ክትትል ማድረግ ፣ በኮሪደር ልማቱ የታየው የስራ ባህል እንዲቀጥል ማድረግ በቀጣይ ትኩረት እንዲሰጣቸው ጠቁመዋል። በቀረበው ሪፖርት ላይ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱ ጥያቄና አስተያየቶች ምላሽ በመስጠት ምክር ቤቱ በሙሉ ድምጽ አጽድቆታል። ምክር ቤቱ በዛሬ መደበኛ ጉባኤው ለከተማ አስተዳደሩ ለ2016 በጀት አመት ተጨማሪ 21 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ያጸደቀ ሲሆን በአባላት ስነ-ምግባር ረቂቅ ደንብ ላይም ተወያይቷል።
በአማራ ክልል የሌማት ትሩፋት ተስፋ ሰጪ ውጤት እያስገኘ መሆኑ ተገለጸ
Apr 26, 2024 61
ደሴ፤ ሚያዝያ 18 /2016(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የሌማት ትሩፋት ምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ምቹ ሁኔታ በመፍጠር ተስፋ ሰጪ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አብዱ ሁሴን ገለጹ። የክልልና የዞን አመራር አባላት በደቡብ ወሎ ዞን ቃሉ ወረዳ የሌማት ትሩፋት ስራዎች እንቅስቃሴን ጎብኝተዋል። በዚህ ወቅት የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አብዱ ሁሴን እንደገለጹት፤ የሌማት ትሩፋት ምግብ ዋስትና ማረጋገጥ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል። ከአርሶ አደሩ በተጨማሪ የከተማው ነዋሪ በአነስተኛ ስፍራ ዶሮ፣ ወተት፣ ማር፣ ዓሳና ስጋ አምርቶ ከመመገብ ባለፈ ምርት ለገበያ በማቅረብ ተስፋ ሰጪና አበረታች ውጤት እያስገኘ መሆኑን ተናግረዋል። ይህን ለማጠናከር ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ሃላፊ ዶክተር ድረስ ሳህሉ በበኩላቸው፤ በህብረተሰቡ የለሙ ተፋሰሶችም ለሌማት ትሩፋት ስራ እንዲውሉ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የሌማት ትሩፋት የዜጎችን ምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባለፈ የዞኑን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት እያገዘ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮንን ናቸው። በዚህም ህብረተሰቡ በትንሽ ስፍራ የእንስሳት ተዋጽኦን ጨምሮ አትክልትና ፍራፍሬ እያመረተ ተጠቃሚ እንዲሆን ድጋፍ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በጉብኝቱ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራር አባላትና ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በሀገር ደረጃ 57 ሚሊዮን የዶሮ ጫጩቶች ተሰራጭተዋል - ግብርና ሚኒስቴር
Apr 26, 2024 70
ሀዋሳ ፤ ሚያዚያ 18/2016 (ኢዜአ):-በሀገር ደረጃ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ57 ሚሊዮን በላይ የዶሮ ጫጩቶች መሰራጨታቸውን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና ዓሣ ሀብት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ፍቅሩ ረጋሳ እንደገለጹት፣ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረገ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ነው። መርሃ ግብሩ ተግባራዊ መደረጉን ተከትሎ በሀገር ደረጃ የሚሰራጩት የዶሮ ጫጩቶች ቁጥር እያደገ መሆኑን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩ ከመጀመሩ በፊት የሚሰራጩት የዶሮ ጫጩቶች መጠን በዓመት ከ20 ሚሊዮን ያልዘለለ እንደነበር አስታውሰዋል። ከመርሃ ግብሩ በኋላ ባለፈው ዓመት ቁጥሩ ወደ 42 ሚሊዮን ማደጉን ጠቁመው፣ በተያዘው በጀት ዓመት ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ 57 ሚሊዮን ጫጩቶች በሀገር ደረጃ ተሰራጭቷል ብለዋል።   ከእንቁላል ምርትና ምርታማነት አኳያም አመርቂ ዕድገት እየታየ መሆኑን ነው ዶክተር ፍቅሩ የገለጹት። ለአብነትም በ2016 በጀት ዓመት ከ6 ነጥብ 2 ቢሊዮን በላይ እንቁላል ለማምረት ታቅዶ በዘጠኝ ወራት 4 ነጥብ 7 ቢሊዮን እንቁላል ማምረት መቻሉን ጠቅሰዋል። የሥነ ምግብ ባለሙያ ዶክተር አንተነህ ኡመር በበኩላቸው እንዳሉት እንደ ሀገር በተጀመረው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር እየተከናወነ ያለው የዶሮ ልማት እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ሕፃን እንቁላል እየተመገበ የሚያድግበት ይሆናል።   በኢትዮጵያ ከ10 ሕፃናት አራቱ የእንስሳት ተዋጽኦና ሌሎች የተመጣጠነ ምግብ ባለማግኘታቸው ለመቀንጨር ችግር ይጋለጣሉ። እንቁላል በአግባቡ የተመገቡ ሕፃናት ካልተመገቡት ጋር ሲነጻጸሩ ለመቀንጨር ችግር የመጋለጥ እድላቸው በተወሰነ ደረጃ ቀንሶ መገኘቱንም ባለሙያው አመልክተዋል። ዶክተር አንተነህ እንዳሉት የተመጣጠነ ምግብ ለሕፃናት መመገብ የነገውን ትውልድ ንቁና ብቁ ለማድረግ ጠቀሜታው የጎላ ነው። እንደ ሀገር በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር እየተመዘገበ ያለው ውጤት ትርጉሙ ብዙ ነው ያሉት ዶክተር አንተነህ፣ መርሃ ግብሩ የቀጣይ ትውልድ ግንባታ ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቅሰዋል። ከዚህ በፊት በነበረው ልምድ በተለይ በገጠር ዶሮን በስፋትና በጥራት የማርባት ልምድ ባለመኖሩ የቤተሰብ ተጠቃሚነት እምብዛም እንደሆነ አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት መንግስት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት በቤተሰብ ደረጃ ዶሮን በብዛት የማርባት ባህል እየተለመደ መምጣቱ ለሌማትም ለገበያም የሚሆን እንቁላል ለማግኘት እያስቻለ ነው ብለዋል ባለሙያው። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የምግብ ሉአላዊነትን ከማረጋገጥ ባለፈ የተመጣጠነ ምግብ በቤተሰብ ደረጃ ለማሟላትና ለሥራ ዕድል ፈጠራ አስተዋጽኦው የጎላ መሆኑ ይገለጻል። የመርሃ ግብሩን የአንድ ዓመት ተኩል አፈጻጸም የገመገመ ሀገራዊ መድረክ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህን ጨምሮ የክልል ርዕሳነ መስተዳድር እና ሌሎች አመራሮች በተገኙበት በሀዋሳ ከተማ መካሄዱ ይታወሳል።  
የመገጭ የመስኖና የመጠጥ ውሃ ግድብ ፕሮጀክት ግንባታን ከፍጻሜ ለማድረስ ርብርብ እንደሚደረግ ተገለጸ
Apr 26, 2024 74
ጎንደር፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- የመገጭ የመስኖና የመጠጥ ውሃ ግድብ ፕሮጀክት ግንባታ ከፍጻሜ ለማድረስ ርብርብ እንደሚደረግ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለጹ። የፌዴራልና የክልሉ ከፍተኛ አመራር አባላት የግድቡን የስራ እንቅስቃሴ ዛሬ ተዘዋውረው ተመልክተዋል፡፡   ርዕሰ መስተዳድሩ በወቅቱ እንደተናገሩት፤ የመገጭ የመስኖና የመጠጥ ውሃ ግድብ ግንባታ ከፍተኛ በጀት ተይዞለት የተጀመረ የልማት ፕሮጀክት ነው፡፡ ፕሮጀክቱ ከአካባቢው መልክዓ ምድር አቀማመጥ አስቸጋሪነት ጀምሮ የግንባታ አቅርቦትና የፋይናንስ እጥረት እንዲሁም በተቋራጮች የአቅም ማነስና ተነሳሽነት ችግሮች ሳቢያ መጓተቶች አጋጥሞት መቆየቱን አውስተዋል፡፡ አሁን ላይ የግንባታው አፈጻጸም 68 በመቶ የደረሰ ሲሆን በተለይ የጎንደር ከተማን የንጹህ መጠጥ ውሃ ችግር በዘላቂነት በመፍታት ትልቅ ተስፋ የተጣለበት ነው ብለዋል፡፡ ፕሮጀክቱ ያጋጠሙትን ማነቆዎች በዝርዝር በመፈተሽ የክልሉና የፌዴራል መንግስት በተናጠልና በጋራ የድርሻቸውን የሚወጡበትን አሰራር እንደሚዘረጋም ተናግረዋል፡፡ በቀጣይ ፕሮጀክቱን ለፍጻሜ ለማብቃት በጋራ ርብርብ እንደሚደረግ ገልጸዋል።   የጎንደር ከተማ አስተዳደር በኢንቨስትመንትና በመሰረተ ልማት ዘርፍ እያከናወናቸው የሚገኙ የልማት ስራዎችም አበረታች መሆናቸውን ርዕሰ መስተዳድሩ አስታውቀዋል፡፡ የአመራር አባላቱ ጉብኝት በተለያዩ ምክንያቶች የተጓተቱ የፌዴራል የልማት ፕሮጀክቶች ለፍጻሜ እንዲበቁ የሚያግዝ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጎንደር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ባዩህ አቡሃይ ናቸው፡፡ እንዲሁም በከተማው በፌዴራል መንግስት ተጀምረው የተጓተቱ የአዘዞ ቡልኮ የኮንክሪት አስፋልት መንገድና የመገጭ የመስኖና የመጠጥ ውሃ ግንባታ ፕሮጀክቶች ችግሮቻቸው ተፈትቶ ለፍጻሜ እንዲበቁ ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል ብለዋል፡፡ በጉብኝቱ የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሀመድን ጨምሮ የክልልና ከተማ አስተዳደሩ የአመራር አባላት የተሳተፉ ሲሆን፤ በከተማው እየተገነቡ የሚገኙ ፕሮጀክቶችን ተመልክተዋል።
የታላቁ የሕዳሴ ግንባታን ከዳር ለማድረስ ኢትዮጵያውያን የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ ቀረበ
Apr 26, 2024 63
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- የታላቁ የሕዳሴ ግንባታን ከዳር ለማድረስ ኢትዮጵያውያን በየተሰማሩበት መስክ የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ጥሪ አቀረበ። 'ዘመናዊነት ያለ ኤሌትሪክ አይታሰብም ' በሚል ርእስ የታተመና 358 ገጾች ያሉት ጥናታዊ መጽሐፍ ለታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ሕዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ተበርክቷል። የጽሕፈት ቤቱ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አረጋዊ በርሔ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታን ከዳር ለማድረስ ኢትዮጵያዊያን በገንዘብና በዕውቀታቸው ሰፊ ድጋፍ እያደረጉ ነው። ከዚህ ውስጥም በገንዘብ 19 ቢሊዮን ብር፤ በአይነት ደግሞ ከ120 ቢሊዮን ብር በላይ ሃብት ከሕዝብ ተሰብስቧል ነው ያሉት። በዛሬው እለት ለጽሕፈት ቤቱ የተበረከተው መጽሐፍ በዘርፉ ያለውን ግንዛቤ ለማሳደግ በጎ አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑን ጠቁመዋል። የመጽሐፉ አዘጋጅ ኢንጂነር አስቀናቸው ገብረየስ በበኩላቸው፤ በአሜሪካን አገር ለበርካታ አመታት በኤሌትሪክ ኃይል ዘርፍ ታላላቅ ስራዎችን በሚያከናውኑ ተቋማት ውስጥ ሲሰሩ መቆየታቸውን ገልፀዋል። ያገኙትን ልምድ መነሻ በማድረግም በስራ ላይ በነበሩበት ወቅት ሲያዘጋጁት የቆዩትን መጽሐፍ 990 ቅጂ ለጽሕፈት ቤቱ ማስረከባቸውን ተናግረዋል። መጽሐፉ በዘርፉ ለሚሰማሩ አካላት፣ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማትና ምርምር ለሚያደርጉ አካላት ዘመናዊ ዕውቀትን የሚያስጨብጥ መሆኑን ጠቅሰዋል።  
በክልሉ ኢንተርፕራይዞች በሙሉ አቅማቸው እንዲያመርቱ የሚደረገው ድጋፍ መጠናከር አለበት -ምክር ቤቱ
Apr 26, 2024 63
አርባ ምንጭ ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የሚገኙ ኢንተርፕራይዞች በሙሉ አቅማቸው ማምረት እንዲችሉ የሚደረገው ድጋፍ መጠናከር እንዳለበት የክልሉ ምክር ቤት አሳሰበ። በክልሉ ኢንዱስትሪ ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጥላሁን ብርሃኑ የተመራ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ቡድን በአርባ ምንጭ ከተማ የኢንተርፕራይዞችን የሥራ እንቅስቃሴ ጎብኝቷል። በዚህን ጊዜ በክልሉ ምክር ቤት የፕላን፣ መሠረተ ልማትና የመንግሥት ሀብት አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ዕንቁ ዮሐንስ እንዳስገነዘቡት ኢንተርፕራይዞችን ማበረታታትና መደገፍ ያስፈልጋል።   ክልሉ ኢንተርፕራይዞች ጎልተው መውጣት እንዲችሉ በሁሉም ዘርፍ የጀመረው ድጋፍ በተቀናጀ መንገድ መጠናከር እንዳለበትም አሳስበዋል። በተለይ ኮርፖሬሽኑ የኢንተርፕራይዞችን አቅም በማሳደግ በክልሉ ያለው የግብርና ምርት እሴት ተጨምሮበት በጥራትና በብዛት ለዓለም ገበያ እንዲቀርብ ተግቶ ሊሰራ እንደሚገባ አመልክተዋል። ምክር ቤቱ ኢንተርፕራይዞቹ በሙሉ አቅማቸው በማምረት የውጭ ምንዛሬ በማዳንና በሥራ ዕድል ፈጠራ የድርሻቸውን እንዲወጡ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። በዓለም ገበያ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመቅረብ የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት አቶ ዕንቁ፣ የኢንዱስትሪዎች ማደግ የኢኮኖሚ ችግርን ለመፍታት ያግዛል ብለዋል። የክልሉ ኢንዱስትሪ ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጥላሁን ብርሃኑ በበኩላቸው ለኢዜአ እንዳሉት፣ በክልሉ የተለያዩ ከተሞች 114 አነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ተደራጅተዋል። ኢንተርፕራይዞቹ ወጪና ተኪ ምርቶችን በማምረት የድርሻውን እየተወጡ ነው ብለዋል። ለአብነትም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ወጪ ምርት ከ700 ሺህ በላይ ዶላር፣ ከተኪ ምርቶች ደግሞ 38 ሚሊዮን ብር ማዳን መቻሉን ነው የጠቀሱት። ኢንተርፕራይዞቹ ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር በኩል ከፍተኛ ድርሻ እንዳላቸው የተናገሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ2 ሺህ 200 ለሚበልጡ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል ተፈጥሯል ብለዋል። አቶ ጥላሁን እንዳሉት በክልሉ የሚገኙት የተቀናጀ ግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ እና አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች በኢኮኖሚና በሥራ ዕድል ፈጠራ አስተዋጿቸው እንዲያድግ መሰረተ ልማት ከማሟላት ጀምሮ ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው ነው። በአርባ ምንጭ ከተማ የ”ጃኖ ዕደ-ጥበብ” ኢንተርፕራይዝ ባለቤት ወጣት ፍሬው ቆንጆ የእጅ ሥራ ምርቶች በዓለም ገበያ ላይ በብዛት ባለመኖራቸው ይህን ዕድል ለመጠቀም ወደ ሥራው መግባቱን ገልጿል።   በዚህም ለቤት ውስጥና ለፋሽን የሚሆን የዕደ-ጥበብ ምርቶችን ለሀገር ውስጥ ከማቅረብ ባለፈ በአሜሪካና በአውሮፓ ገበያዎች በማቅረብ ተጠቃሚ እየሆነ መምጣቱን ነው የተናገረው። ''የአባቶችን የዕደ-ጥበብ አሠራር ባህል ወደ አሁኑ ትውልድ እያስተላለፍን እንገኛለን'' ያለው ወጣቱ፣ ኢንተርፕራይዙ በአሁኑ ወቅት ለ80 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጿል። በአርባ ምንጭ ከተማ የሚገኘው ”ያላ ወተት ማቀነባበሪያ” ፋብሪካ ባለቤት አቶ ዓለማየሁ እሥራኤል በፋብሪካው ቺዝ፣ ክሬም፣ ቅቤ፣ እርጎና ወተት በማምረት ላይ ናቸው።   ፋብሪካው በጋሞ ዞን ሁሉም ወረዳዎችና አጎራባች ዞኖች የወተት ማሰባሰቢያ ማዕከላት በማቋቋም ለበርካታ ወገኖች የሥራ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። ፋብሪካው ከሁለት ወራት በኋላ በሙሉ አቅሙ ወደ ምርት ሲገባ በወተት አቅርቦት ላይ የሚስተዋለውን እጥረት በማቃለል የውጭ ምንዛሬን ለማስቀረት የድርሻውን እንደሚወጣ አቶ አለማየሁ ገልጸዋል።  
ለትንሣኤ በዓል ጤናማ የገበያ ስርጭትና ዋጋ እንዲኖር በትኩረት እየተሰራ ነው - የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ
Apr 26, 2024 78
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- ለትንሣኤ በዓል የምርት አቅርቦትን በማሳደግ የዋጋ መረጋጋት እንዲሰፍን ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ ገለጸ። በኅብረተሰቡ ላይ እየደረሰ ያለውን የኑሮ ውድነትና የዋጋ ንረት ጫና ለመከላከል ግብረ ሃይል አደራጅቶ ስራ መጀመሩን ቢሮው ገልጿል። ለትንሣኤ በዓል በዋናነት በጀሞ፣ በላፍቶ፣ በአቃቂ፣ በለሚ ኩራና በኮልፌ ሁለገብ የገበያ ማዕከላት እንዲሁም በ188 የእሁድ ገበያዎች የዋጋ መረጋጋት እንደሚታይ ቢሮው ገልጿል። በቢሮው የንግድና ግብይት ዘርፍ ምክትል ቢሮ ሃላፊ አቶ ፍስሐ ጥበቡ ገበያው የተረጋጋ እንዲሆን ከነገ ጀምሮ በእሁድ ገበያዎች ምርቶች በስፋት እንዲገቡ ይደረጋል ብለዋል። በመዲናዋ የነበረው የዋጋ ንረት አሁን ላይ እየተረጋጋ መምጣቱንም ነው ምክትል ቢሮ ሀላፊው የጠቀሱት፡፡ በመንግሥት የገበያ ማዕከላትና በእሁድ ገበያዎች እየተሸጡ ያሉ ምርቶች ከ15 እስከ 20 በመቶ የዋጋ ቅናሽ እንዲኖራቸው መደረጉ ለገበያ መረጋጋት አስተዋጽኦ ማበርከቱን ምክትል የቢሮ ሃላፊው አብራርተዋል። በለሚ ኩራ፣ በኮልፌ እና በአቃቂ ቃሊቲ ዘመናዊ የመንግሥት የገበያ ማዕከላትም ከሰኞ ጀምሮ ከ154 በላይ የኅብረት ሥራ ማኅበራት የሚሳተፉበት የባዛርና የንግድ ትርዒት እንደሚካሄድ ተናግረዋል። በመንግሥት የገበያ ማዕከላትና የእሁድ ገበያዎች ከ76 በላይ አርሶ አደሮችና ከአንድ መቶ በላይ ኢንተርፕራይዞች ምርቶቻቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ ለኅብረተሰቡ እንደሚያቀርቡ ጨምረው ገልጸዋል። የአዲስ አበባ የከተማ ግብርናና አርሶ አደር ኮሚሽንም የግብርና ውጤቶቹን ለኅብረተሰቡ እንደሚያቀርብ እንዲሁ። የቁም እንስሳት በሚሸጡባቸው በአቃቂ፣ በየካ ካራአሎ፣ ሸጎሌ፣ በአዲስ ከተማ ብርጭቆ ፋብሪካ አካባቢዎች ጤናማ የገበያ ሥርጭትና ግብይት እንዲኖር በቂ ዝግጅት መደረጉን አቶ ፍስሐ አመላክተዋል። ደረጃቸውን ያልጠበቁ ምርቶች በግብይት ውስጥ እንዳይገቡና የዋጋ ንረት እንዳይከሰት ጥብቅ የሆነ ክትትልና ቁጥጥር ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እንደሚሰራም ጠቁመዋል። ከበዓሉ ጋር በተያያዘ ሊስተዋሉ የሚችሉ ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የክትትልና የቁጥጥር ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አመልክተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም