ኢኮኖሚ
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሰዎች ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ የሚያስችል ነው -አምባሳደሮች
Apr 30, 2025 47
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ሰዎች ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙና በርካታ አገልግሎቶችን በፍጥነት እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች ተናገሩ። የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀስላሴን ጨምሮ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫን ጎብኝተዋል።   መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ማዕከል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተመርቆ ወደ ስራ መግባቱ ይታወሳል። በዛሬው እለትም የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀስላሴ እንዲሁም የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች ማዕከሉን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ መሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት አይን ገላጭ ነው ሲሉ ተናግረዋል። ማዕከሉ የኢትዮጵያ መንግሥት በቴክኖሎጂ የተደገፈ የአገልግሎት ማዕከል ለመፍጠር ምን ዓይነት ዝርዝር ዕቅድና ጥናት እንዳደረገ የሚያሳይ መሆኑንም ገልጸዋል። ቴክኖሎጂው በኢትዮጵያዊያን መልማቱ አስደናቂ መሆኑን ገልጸው፥ ይህም የመረጃ ሉአላዊነትን የሚያረጋግጥ እንደሆነም ጠቁመዋል። በማዕከሉ የተገነቡ መሰረተ ልማቶች በአጠቃላይ አስደሳች መሆናቸውን ጠቅሰው፥ አገልግሎቱም ፈጣን መሆኑን ለመመልከት መቻላቸውን ተናግረዋል። ማዕከሉ የአገልግሎት ተደራሽነት የሚያረጋግጥ መሆኑንም አክለዋል።   በኢትዮጵያ የሩስያ አምባሳደር ኤቭጌኒ ቴርኪን በበኩላቸው፥ በማዕከሉ የተመለከቱት ስራ አስደናቂ መሆኑን ገልጸዋል። ማካካስ ከማይቻሉ ነገሮች መካከል ጊዜ አንዱ መሆኑን የገለጹት አምባሳደሩ ሰዎች ጊዜያቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ የሚያስችል ማዕከል መሆኑን ተናግረዋል።
በአዲስ አበባ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ሰፋፊ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው -ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 30, 2025 44
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦በመዲናዋ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያስችሉ ስፋፊ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ስብሰባውን አካሂዷል።   የምክር ቤቱ አባላት በየመስኩ ማብራሪያ የሚሹ ጥያቄዎችን አቅርበው በከንቲባ አዳነች አቤቤ እና የሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቷል። ከመሰረተ ልማት አቅርቦት፣ የኑሮ ውድነት ማረጋጋት እንዲሁም አገልግሎት አሰጣጥ ላይ መልካም ውጤቶች መገኘቱን ያነሱት የምክር ቤቱ አባላት ዘላቂነት ላይ ይበልጥ ሊሰራ እንደሚገባም ነው ያነሱት። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በሰጡት ማብራሪያ፥ ከመሰረተ ልማት አቅርቦትና የኑሮ ውድነት ከማረጋጋት እንዲሁም አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ በማብራሪያቸውም ኑሮ ውድነትን ለመቀነስ በምርት አቅርቦት እንዲሁም በከተማ ግብርና ላይ ሰፋፊ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል ። ከምርት አቅርቦት አኳያም በመዲናዋ በተገነቡ የገበያ ማዕከላት ምርትን ከአርሶ አደሩ በቀጥታ በመቀበል ለሸማቾች በተመጣጣኝ ዋጋ ተደራሽ እየተደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህም በተጨማሪ በመዲናዋ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማና ለሚኩራ ክፍለ ከተማ ቁጥር 2 የገበያ ማዕከላትን ወደ ሥራ ለማስገባት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ ወደ ስራ የሚገቡ የገበያ ማዕከላት ገበያውን የማረጋጋት አቅምን ይበልጥ የሚያሳድጉ መሆናቸውንም አስታውቀዋል። ወደ 1 ሚሊዮን የሚጠጉ ተማሪዎች የትምህርት ቤት ምገባ መርሃ ግብር ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉን ገልጸው 35 ሺህ አረጋዊያንን እና ለተለያዩ ችግሮች የተጋለጡ ዜጎች የምገባ መርሃ ግብር ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በመዲናዋ የሚሰጠው የትራንስፖርት አገልግሎት ዜጎችን በማይጎዳ መልኩ አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን ገልጸው፤ ከተማ አስተዳደሩ በዓመት ከ 3 ቢሊዮን ብር በላይ ድጎማ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። ከንቲባዋ እንደገለጹት፥ በኮሪደር ልማት ምክንያት ለተነሱ ነዋሪዎች 9 ሺህ 700 ቤቶች ተገንብተው ተደራሽ የተደረጉ ሲሆን ለአቅመ ደካማ ዜጎችም ቤቶችን በማደስና በመገንባት የማቅረብ ሥራዎች በተሳካ መልኩ ተከናውነዋል። 347 አገልግሎቶችን ወደ ዲጂታል መቀየራቸውን የገለጹት ከንቲባ አዳነች አገልግሎትን በዲጂታል የመስጠቱ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል። የተሳለጠ አገልግሎትን ለነዋሪዎች ተደራሽ ከማድረግ አኳያም በርካታ አገልግሎቶችን በአንድ ማዕከል ለመስጠት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። ከመዲናዋ እድገት ጋር ተያይዞ የውሃ አቅርቦት ፍላጎት እየጨመረ መሆኑን ጠቅሰው፤ አቅርቦትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃንጥራር አባይ በበኩላቸው፥ የኮሪደር ልማቱ በሁሉም አካባቢዎች ደረጃ በደረጃ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ምክር ቤቱ ለ2017 በጀት ዓመት ከ11 ቢሊዮን 556 ሚሊዮን ብር በላይ ተጨማሪ በጀትንና ለተለያዩ የስራ ሃላፊዎች ሹመት በማጽደቅ ተጠናቋል።
ፕሮጀክቱ 12 ሺህ የአንድ ቀን የዶሮ ጫጩቶችን አሰራጨ
Apr 30, 2025 45
ሀዋሳ ፤ሚያዝያ 22/2017 (ኢዜአ)፡- ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ የሻሎ ቅድመ ወላጅ የዶሮ ልማት ፕሮጀክት ያራባቸውን 12 ሺህ የአንድ ቀን ጫጩቶች አሰራጨ። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት በሀገር ደረጃ የተያዘውን የዶሮ እርባታ ለማስፋፋት ተግዳሮት ከሆኑት አንዱ በየጊዜው የአንድ ቀን ጫጩቶችን ከውጪ ማስገባት ነበር። ችግሩን ለመፍታት ከተያዙ አቅጣጫዎች ውስጥ አንዱ የቅድመ ወላጅ ዶሮዎችን በሀገር ውስጥ በማርባት ማሰራጨት መሆኑን ጠቁመዋል። የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብርን ለማሳካት በተያዘው አቅጣጫ መሰረት ቅድመ ወላጅ ዶሮዎችን በሀገር ውስጥ አባዝቶ ለአርቢ ማዕከላት ለማሰራጨት ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ሀላፊነት ወስዶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ዛሬ ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰራጩት የአንድ ቀን የዶሮ ጫጩቶችን የሚረከቡ አባዥ ማዕከላት አስፈላጊውን መስፈርት አሟልተው የተመረጡ መሆናቸውን አስታውቀዋል። በዚህም ዛሬ በሲዳማ ክልል እንስሳትና አሣ ሀብት ልማት ቢሮና በአላጌ ግብርና ኮሌጅ ስር ላሉ ማእከላት 12 ሺህ የአንድ ቀን የዶሮ ጫጩቶችን ማስረከብ እንደተቻለ ገልጸዋል። በሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ የአግሮ ክላስተር ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፈለቀ ታደሰ እንደገለጹት ከስምንት ወራት በፊት ከሀንጋሪ ከገቡ 10 ሺህ ቅድመ ወላጅ የዶሮ ዝርያዎች የተገኙ 12 ሺህ የአንድ ቀን የዶሮ ጫጩቶችን ለመጀመሪያ ጊዜ ማሰራጨት መጀመሩን ተናግረዋል። ፕሮጀክቱ ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመቀናጀት ከዛሬ ጀምሮ በየሳምንቱ 12 ሺህ የአንድ ቀን የዶሮ ጫጩቶችን ለተመረጡ አባዥ ማዕከላት እንደሚሰራጭ አመላክተዋል።  
በመተማ ወረዳ የሰሊጥና የአኩሪ አተርን ምርታማነት ለማሳደግ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Apr 30, 2025 43
ገንዳ ውሃ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል መተማ ወረዳ በመኸር ሰብል የሰሊጥና የአኩሪ አተርን ምርታማነት ለማሳደግ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የምዕራብ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የአካባቢው አርሶ አደሮች በበኩላቸው ለዘንድሮው መኸር እርሻ የተሻለ ምርት ለማግኘት የሚያስችል የመሬት ዝግጅት እያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ቡድን መሪ ጌትነት ካሳሁን፤ በዞኑ ለመኸር አዝመራው እየተደረገ ያለውን ዝግጅት በማስመልከት ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በዞኑ በተለይም የሰሊጥ፣ አኩሪ አተር፣ ማሽላ፣ ጥጥ፣ ማሾ እና ሌሎችም ሰብሎችን ማምረት የሚያስችል ምቹ ሁኔታ መኖሩን ገልጸዋል። በዚሁ መሰረት በ2017/18 የምርት ዘመን 530 ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ከታቀደው እስካሁን ከ345 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለዘር ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል። በተያዘው የመኸር ወቅትም 12 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል ምርት የማግኘት ግብ መያዙን አንስተው ከመሬት ዝግጅት ባለፈ የግብርና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ግብዓቶችን የማቅረብና የሜካናይዜሽን እርሻን የማጠናከር ስራ ትኩረት የተሰጠው መሆኑን አንስተዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን መተማ ወረዳ አርሶ አደር ጋሻው ፈረደ፤ በዘንድሮው የመኸር ወቅት የመሬት ዝግጅት በማድረግ የተሻለ ምርት ለማግኘት ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። አርሶ አደሩ 10 ሄክታር መሬታቸውን በሰሊጥ፣አኩሪ አተር፣ማሽላና የጤፍ አዝእርት ለመሸፈን ያቀዱ መሆኑንም ተናግረዋል። በመተማ ወረዳ በግብርና ኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰማሩት አቶ አብርሃም ሲሳይ በበኩላቸው፤ በመኸሩ ከ60 ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ለዘር ዝግጁ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። በዞኑ ባለፈው ዓመት የምርት ዘመን 521 ሺህ ሄክታር መሬት በማልማት 8 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል ምርት መገኘቱን መረጃዎች ይጠቁማሉ።
የሎጂስቲክስ ዘርፉን ይበልጥ ለማሳደግና ለማዘመን እየተሰራ ነው -ሚኒስትር ዴኤታ ደንጌ ቦሩ
Apr 30, 2025 35
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የሎጂስቲክስ ሴክተሩ የሚሠጠውን አገልግሎት ይበልጥ ለማሳደግና ለማዘመን እየተሰራ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር ዴኤታ ደንጌ ቦሩ ገለጹ። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር የሎጅስቲክስ ሴክተሩ አገልግሎት አሰጣጥ ላይ በዘርፉ ከተሰማሩ የግል ተቋማት ሃላፊዎች ጋር ምክክር አካሂዷል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታው ደንጌ ቦሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ የሎጂስቲክስ ሴክተሩ የሚሠጠውን አገልግሎት ለማሳደግና ለማዘመን የተጠናከሩ ስራዎች በመከናወን ላይ ናቸው።   በተለይም ዘርፉ እያደገ የመጣውን የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ማስተናገድ እንዲችል አገልግሎት አሰጣጡን ማሳደግ የሚያስችል ስራዎች በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀዋል። እንዲሁም በመስኩ የተሰማሩ ኩባንያዎች የሚያነሷቸውን ጥያቄዎች በየደረጃው ምላሽ እንዲያገኙ በማድረግ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም ሴክተሩ ፈጣን፣ቀልጣፋና ወጪ ቆጣቢ እንዲሆን በቅንጅት መስራት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አማካሪ መንግስቴ ኃይለማርያም (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በሎጂስቲክስ ዘርፉ ተመዝግበው የሚሰሩ አካላት ያላቸውን ተሳትፎ ለማየትና ለማሳደግም ምክክሩ መዘጋጀቱን ጠቅሰዋል። ባለፉት አምስት አመታት በሎጂስቲክስ ዘርፉ ላይ ለውጦች የተመዘገቡ ሲሆን በቀጣይም በመስኩ የተሰማሩ ተቋማት የዘርፉን ተለዋዋጭ ባሕሪ ታሳቢ በማድረግ መስራት እንዳለባቸውም አንስተዋል። የኢትዮ ሎጂስቲክስ አሶሴሽን ፕሬዚዳንት ኤልሳቤጥ ጌታሁን በበኩላቸው፤ የሎጂስቲክስ ዘርፉን ለማሳደግ ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ጋር የሚከናወኑ ተግባራት ለውጥ እያመጡ ነው ብለዋል።
በጌዴኦ ዞን ያረጁ የቡና ዛፎችን ነቅሎ በተሻሻለ ዝርያ የመተካት ሂደት ምርታማነት እንዲጨምር አድርጓል
Apr 30, 2025 38
ዲላ፤ ሚያዝያ 22/2017 (ኢዜአ)፡- በጌዴኦ ዞን ያረጁ የቡና ዛፎችን ነቅሎ በተሻሻለ ዝርያ የመተካት ሂደት የምርት ጊዜን ከማሳጠር ባለፈ ምርታማነት እንዲጨምር እያደረገ መሆኑ ተገለጸ። በዞኑ የዘንድሮ የቡና ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ዛሬ በኮቾሬ ወረዳ ሐንጫቢ ቀበሌ ተካሄዷል።   የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት በዞኑ ከ75 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በቡና ተክል የተሸፈነ ነው። በዞኑ ያረጀና በበሽታ የተጠቃ ቡና ለምርታማነት ማነቆ መሆኑን ጠቅሰው ችግሩን ለማቃለል በቡና እድሳት ላይ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   በተለይ ያረጀ ቡና ነቅሎ በተሻሻለ ዝርያ የመተካት ጥረት የምርት ጊዜን ወደ ሁለት ዓመት ከማሳጠር ባለፈ በሞዴል አርሶ አደሮች ማሳ ከፍተኛ ምርት እያስገኘ መሆኑን አመልክተዋል። በዞኑ ከ4 ሺህ 200 ሄክታር በላይ ማሳ ላይ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና ችግኞች ተከላ መጀመሩን የገለጹት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ ታጠቅ ዶሪ ናቸው። በዞኑ ለዘንድሮ የቡና ተከላም ከ11 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኝ መዘጋጀቱን አስታውቀዋል ። የኮቾሬ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ጌታቸው ታሪኩ በበኩላቸው "በወረዳው በተያዘው ዓመት ከ525 ሄክታር በላይ ነባር ማሳ ላይ ያረጁ የቡና ዛፎችን በማንሳት በተሻሻሉ ዝርያዎች ለመተካት ተግባራዊ እንቅስቃሴ ተጀምሯል" ብለዋል። በተለይ ሐንጫቢን ጨምሮ የቡና ዛፍ እርጅና በስፋት በሚስተዋልባቸው አራት ቀበሌዎች ያረጀ ቡና በኩታ ገጠም የማንሳቱ ተግባር በትኩረት መከናወኑን ገልጸዋል። በወረዳው የሐንጫቢ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ውዴ መላኩ በበኩላቸው ''ያረጀ አባት ቡና ይዞ መቀመጥ ትርፉ ድካም ነው” ብለዋል። ከአንድ ሄክታር ማሳቸው ላይ ያረጀ የቡና ዛፍ በመንቀልና ከአንድ ሺህ በላይ ጉድጓዶች በማዘጋጀት የተሻሻሉ የቡና ዝርያ የመተካት ስራ መጀመራቸውን ተናግረዋል።  
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የመንግስትን የአገልግሎት አሰጣጥ ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር ነው-ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ
Apr 30, 2025 46
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት የመንግስትን የአገልግሎት አሰጣጥ ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር መሆኑን የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ገለጹ። የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴን ጨምሮ የተለያዩ አገራት አምባሳደሮች መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫን ጎብኝተዋል። መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫ ማዕከል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተመርቆ ወደ ስራ መግባቱ ይታወሳል። ማዕከሉ 12 ተቋማትን እና ከ41 በላይ አገልግሎትን በአንድ ህንፃ ማግኘት የሚያስችል ነው። የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ እንዲሁም የተለያዩ አገራት አምባሳደሮች መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።   ፕሬዚዳንት ታዬ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ መንግስታት ለህዝባቸው የተቀላጠፈ እና የተሳለጠ አገልግሎት የመስጠት ግዴታም ሀላፊነትም አለባቸው። ይህ አዲስ ሁሉን አቀፍ የሆነ በአንድ ቦታ በርካታ አገልግሎት መስጠት የተጀመረው ስራ የኢትዮጵያን የህዝብ አገልግሎት ከፍ የሚያደርግ መሆኑን ጠቁመዋል። የመንግስት ተአማኒነት የሚለካው በሚሰጠው አገልግሎት መሆኑን ጠቁመው፤ ከዋነኛ መመዘኛዎቹ መካከልም አንዱ መሆኑን አመላክተዋል። በኢትዮጵያ በመንግስት አገልግሎት ዙሪያ ያለው ተሞክሮ የሚያኩራራ አለመሆኑን ያወሱት ፕሬዚዳንት ታዬ፤ ማዕከሉ ብልሹ አሰራርን በማስቀረት እንግልትን የሚያስወግድ መሆኑን ተናግረዋል። ማዕከሉ ህዝብ የሚገባውን አገልግሎት ያገኝ ዘንድ የተገነባ ትልቅ ስራ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተለያዩ ዓለማት ስንመለከት የምንቀናበትን ስራ በሀገራችን ተመልክተነዋል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ይህንን ላከናወኑ ምስጋና አቅርበዋል። በራስ ባለሙያዎች በአጭር ጊዜ ወደስራ ማስገባትም ትልቅ እመርታ መሆኑን አንስተዋል። ማዕከሉ የህዝብ እንግልትን የሚያስወግድ መሆኑን ለማሳወቅም ሰፊ የተግባቦት ስራ መሰራት እንዳለበት አስገንዝበዋል።
ኤክስፖው የኢትዮጵያን ተወዳዳሪነት የሚያሳዩ አዳዲስ የኢንዱስትሪ ቴክኖሎጂዎች የሚቀርቡበት ነው- ሚኒስትር መላኩ አለበል
Apr 30, 2025 41
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ የኢትዮጵያን ተወዳዳሪነት የሚያሳዩ አዳዲስ የኢንዱስትሪ ቴክኖሎጂዎች የሚቀርቡበት መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በመጪው ቅዳሜ በይፋ የሚከፈተውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ አስመልክቶ ለጋዜጠኞች ማብራሪያ ሰጥተዋል። በዚሁ ወቅት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከተጀመረ ጀምሮ ኢንዱስትሪዎች ያጋጥማቸው የነበሩ ችግሮች ደረጃ በደረጃ እንዲፈቱና የማምረት አቅማቸው እንዲጎለብት ማድረጉን አንስተዋል። ንቅናቄው የአገር ውስጥ ምርት አጠቃቀም ላይም ሰፊ ለውጦች መምጣቱን ገልጸዋል። 3ኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ በመጪው ቅዳሜ ሚያዝያ 25 ቀን 2017 ዓ-ም በይፋ እንደሚጀመር ገልጸው፤ የኢትዮጵያን ምርቶች ማስተዋወቅና ተጨማሪ የገበያ ዕድሎችን ማስፋት የኤክስፖው ዋና ዓላማ ነው ብለዋል። የገበያ ትስስሮችን መፍጠርና የምርት ጥራትን ለማሻሻልም ጉልህ ሚና ይኖረዋል ነው ያሉት። ፈጠራን ማበረታታትም አንዱ የኤክስፖው ዓላማ መሆኑን ጠቅሰው፤ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የልምድ ልውውጥ መፍጠርም ዋነኛ ግቡ መሆኑን ተናግረዋል። በኤክስፖው ኢትዮጵያን ተወዳዳሪ የሚያደርጉና በአይነታቸው ልዩ የሆኑ የኢንዱስትሪ ቴክኖሎጂዎች እንደሚቀርቡም ነው የገለጹት። ከኤክስፖው አስቀድሞ በተለያዩ ክልሎች የተደረጉ ኤግዚቢሽንና ባዛሮች እንዲሁም የኢትዮጵያ ታምርት የ10ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ የኢትዮጵያን ምርት በማስተዋወቅ በኩል ጉልህ ሚና ነበራቸው ብለዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶችን ከማስተዋወቅ ባለፈ የተለያዩ የፓናል ውይይቶች፣ የምርት ልማት ውድድሮች፣የተሻለ አፈፃፀም ላላቸው ኢንዱስትሪዎች የዕውቅና ፕሮግራም እና ሌሎችም መርሃ-ግብሮች ይከናወናሉ። በአዲስ አለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ለአምስት ቀናት የሚካሄደውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ከ120 ሺህ በላይ የአገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች እንደሚገኙም በመግለጫው ተብራርቷል። በኤክስፖው 288 ኢንዱስትሪዎች የሚሳተፉ ሲሆን ከአራት ቢሊዮን ብር በላይ ግብይት ይፈፀማል ተብሎ ይጠበቃል። ኤክስፖውን ሁሉም ዜጋ እንዲጎበኘውና የኢትዮጵያን ምርት እንዲገዛ ሚኒስትሩ ጥሪ አቅርበዋል።        
በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር የተከናወኑ የሰላምና የልማት ስራዎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉና ውጤታማ ናቸው
Apr 30, 2025 37
በደብረ ብርሃን፤ ሚያዚያ 22/2017 (ኢዜአ)፡- በደብረ ብርሃን ከተማ ሰላምን በማጽናት የተከናወኑ የሰላምና የልማት ስራዎች የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ውጤታማ መሆናቸውን የከተማ አስተዳደሩ ምክር ቤት አስታወቀ። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት የዘጠኝ ወራት እቅድ አፈጻጸም የግምገማ መድረክ እየተካሄደ ነው።   የምክር ቤቱ ዋና አፈ-ጉባዔ አቶ መንግስቱ ቤተ በጉባዔው ላይ እንደገለጹት በከተማ አስተዳደሩ የተከናወኑ የሰላምና የልማት ስራዎች አበረታች ውጤት ያስመዘገቡ ናቸው። የከተማ አስተዳደሩ የክላስተር አደረጃጀት ፈጥሮ የሚካሄዱ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎችን መምራት፣ መደገፍና መቆጣጠር በመቻሉ አበረታች ውጤት እንዲመዘገብ አስችሏል ብለዋል። የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በከተማዋ እየተካሄዱ ያሉ የአስፋልት፣ የኮብል ስቶንና ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎች አፈጻጸም የተሻለ መሆኑን አረጋግጠዋል። ከዚህ በተጨማሪም የህብረተሰቡን ጥያቄ በመለየትና አፋጣኝ መፍትሄ በመስጠት የመልካም አስተዳደር ችግርን ለመቅረፍ የተሰራው ስራ መልካም ውጤት የታየበት ነው ብለዋል።   የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት ባቀረቡት ሪፖርት ላይ እንደገለጹት አስተዳደሩ ማህበረሰቡን በማስተባበር ያከናወነው ሰላምን የማስፈንና ልማትን የማረጋገጥ ስራ ስኬታማ ነው። ባለፉት ዘጠኝ ወራት የኮሪደር ልማት፣ የመብራትና የውሃ መስመር ማስፋፋት፣ የውስጥ ለውስጥ መንገድና ሌሎች የልማት ስራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል። የከተማው ማህበረሰብም የልማት ስራዎቹን ለማከናወን የሚያስችል ከ160 ሚሊዮን ብር በላይ አስተዋጽኦ ማድረጉን አስረድተዋል። በተለይም በ83 ማህበራት ለተደራጁ የከተማዋ ነዋሪዎች የቤት መስሪያ ቦታ መሰጠቱ የከተማዋን ነዋሪዎች የረጅም ጊዜ ጥያቄ የፈታ ስኬታማ ስራ መሆኑን አረጋግጠዋል። በተጨማሪም ሰላምን ከማስፈን ጎን ለጎን በኢንቨስትመንት፣ በከተማ ግብርና፣ በንግድ፣ የኑሮ ውድነትን በመቀነስና በሌሎች ተግባራት ውጤታማ ስራ እንደተሰራ አብራርተዋል። በዘጠኝ ወራት ውስጥ ለ14 ሺህ 22 ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር መቻሉን ጠቁመው ለስራ እድል ተጠቃሚዎችም የመስሪያና የመሸጫ ቦታ፣ ብድርና ሌሎች ድጋፎች መደረጋቸውን ተናግረዋል።  
ዲፕሎማቶች የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ጎበኙ
Apr 30, 2025 42
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ ተቀማጭነታቸውን ያደረጉ የዲፕሎማቲክ ማኀበረሰብ አባላት ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በተገኙበት መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታዎች አምባሳደር ብርሃኑ ጸጋዬ እና አምባሳደር ሃደራ አበራ በተገኙበት ጉብኝት አድርገዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለዜጎች የሚሰጠውን አገልግሎት ፣ አሰራር ስልቶች በተመለከተ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የቆንስላ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር ሲራጅ ረሺድ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በቀጣይም የአገልግሎት አሰጣጡን በማሻሻል የተሟላ እና ቀልጣፋ ዘመናዊ አገልግሎት ለመስጠት ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራ ተገልጿል። በመንግሥት የሚሰጡ አገልግሎቶች በኤሌክትሮኒክ በመተጋዝ 12 ተቋማት በአንድ ጣሪያ ሥር 40 የተለያዩ አገልግሎቶችን መስጠት መጀመራቸው ይታወቃል። ይህም ዜጎች ጊዜያቸውን እንዲቆጥቡ እና አገልግሎቶችን በተሻለ ውጤታማ መንገድ እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመረጃው አመልክቷል።
ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅትን በአባልነት እንድትቀላቀል አሜሪካ ድጋፍ ታደርጋለች
Apr 30, 2025 42
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ አሜሪካ ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅትን በአባልነት እንድትቀላቀል ድጋፍ እንደምታደርግ የአሜሪካ የንግድ ፅህፈት ቤት ተወካይ ኒል ቤክ ገለጹ። ኢትዮጵያ በተሳካ ሁኔታ ከዓለም አቀፉ የግብይት ሥርዓት ጋር መዋሃድ የአሜሪካ ፍላጎት ነውም ብለዋል። የዓለም ባንክ ግሩፕ እና የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዓመታዊ የፀደይ ወቅት ስብስባ በዋሺንግተን ዲሲ ተካሄዷል። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) በአሜሪካ የንግድ ፅህፈት ቤት የዓለም ንግድ ድርጅት እና የባለ ብዙ ወገን ጉዳዮች ረዳት ተወካይ ኔል ቤክ ጋር ተወያይተዋል።   በውይይቱ ሚኒስትር ዴኤታው ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅትን በአባልነት ለመቀላቀል እያደረገች ያለውን ከፍተኛ ጥረት አስመልክተው ገለጻ አድርገዋል። እ.ኤ.አ. በማርች 2026 ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን የሚያስፈልጉትን መስፈርቶች ለማሟላት ቁርጠኛ መሆኗን ገልጸዋል። ኔል ቤክ ኢትዮጵያ የዓለም የንግድ ድርጅት አባል ለመሆን እያከናወነች ያለውን ከፍተኛ ጥረት አድንቀው፤ የዓለም ንግድ ድርጅትን በአባልነት እንድትቀላቀል አሜሪካ ድጋፍ እንደምታደርግ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በተሳካ ሁኔታ ከዓለም አቀፉ የግብይት ሥርዓት ጋር መዋሃድ የአሜሪካ ፍላጎት ነው ብለዋል። ሁለቱ ወገኖች ኢትዮጵያ የዓለም ንግድ ድርጅት አባል ለመሆን በምታደርገው ጉዞ ላይ ትብብራቸውን ለመቀጠልና አጋርነታቸውን ለማጠናከር መስማማታቸውን ኢዜአ ከገንዘብ ሚኒስቴር ያገኘው መረጃ አመልክቷል።
የአዳማ ከተማን የኢንቨስትመንት ፍሰት ይበልጥ ለማሳለጥ የአንድ ማዕከልና ዲጂታል አገልግሎት ተደራሽ እየተደረገ ነው
Apr 30, 2025 33
አዳማ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የአዳማ ከተማን የኢንቨስትመንት ፍሰት ይበልጥ ለማሳለጥ የአንድ ማዕከልና ዲጂታል አገልግሎት ተደራሽ እየተደረገ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ ገለፁ። ከተማ አስተዳደሩ ከባለሃብቶች ጋር በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመቅረፍና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ ላይ ምክክር አድርጓል።   ከንቲባው በወቅቱ እንደገለፁት፥ መንግሥት የአሰራርና የህግ ማዕቀፎችን በአዲስ መልክ በማዘጋጀት የኢንቨስትመንት ፍሰቱ ሁሉንም ባማከለ መልኩ እንዲከናወን እየተደረገ ነው። ባለፉት ዓመታት በአስተዳደሩ በርካታ ባለሀብቶች ወደ ኢንቨስትመንት መግባታቸውን ገልጸው፥ ውጤታማነታቸውም የተሻለ መሆኑን ተናግረዋል። ከተማ አስተዳደሩ ዘመናዊ የመሬት አስተዳደር ስርዓት እውን በመደረጉ፣በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘና ሌሎች ዘመናዊ አሰራሮች ተግባራዊ መደረጋቸው ለባለሀብቶች ምቹ ሁኔታ እየተፈጠረ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተጠቃሽ መሆኑን የገለፁት አቶ ሀይሉ፤ የመሰረተ ልማት አቅርቦትም የተሻለ እንዲሆን የተለያዩ ስራዎች መከናወናቸውን ነው የገለጹት። ከመሰረተ ልማቶቹ መካከል አዳማ ወንጂ የአስፋልት መንገድ፣ የአዳማ አዋሽ መልካሣ የአስፋልት መንገድ ደረጃ የማሻሻል ስራ መሰራቱን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የመብራት፣ የውሃ፣ የመሬትና የብድር አቅርቦት ዙሪያ ቀልጣፋ የአገልግሎት አሰጣጥ እንዲኖር መደረጉንም ነው የተናገሩት። አስተዳደሩ በሌብነትና ብልሹ አሰራር ውስጥ የተሳተፉ አመራሮች፣ የስራ ሀላፊዎችና ሰራተኞች ላይ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ጠቅሰዋል። አያይዘውም፥ መሬት አጥረው በሚያስቀምጡ ባለሃብቶች፣የተጓተቱ ፕሮጀክቶችና የገነቡትን የኢንዱስትሪ ሼዶች ለመጋዘን አገልግሎት ያዋሉ ባለሃብቶች ላይ ጠንካራ እርምጃ ይወሰዳል ብለዋል። የአዳማ ከተማ ባለሃብቶች ፎረም ሰብሳቢና የአዳማ ቆሮቆሮ ፋብሪካ ባለቤት አቶ አብዱልሃኪም ሙሐመድ በበኩላቸው፥ ፎረሙ የባለሀብቶችን ጥያቄዎች ለመመለስ ከአስተዳድሩ ጋር በትብብር እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ የኢንዱስትሪዎች ምርታማነት እንዲያድግና ኢንቨስትመንት እንዲጨምር አስችሏል- ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Apr 30, 2025 46
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በአማራ ክልል የኢንዱስትሪዎችን ምርትና ምርታማነት ከማሳደጉም በተጨማሪ ኢንቨስትመንት እንዲስፋፋ ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢንዱስትሪ ዘርፉን ማነቆዎች በመፍታት ምርታማነታቸውን ማሳደግ የሚያስችለውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን ሚያዝያ 2014 ዓ.ም ማስጀመራቸው ይታወሳል። ሀገራዊ ንቅናቄው የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉን ውስብስብ ችግሮች በቅንጅት በመፍታት ተወዳዳሪና ምርታማ ማድረግ አስችሏል። በዚህም ከውጭ ይገቡ የነበሩ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በማምረት ወጪን በመቀነስ የምርት ጥራትና አቅርቦትን ያሳለጠ ውጤታማ ንቅናቄ ሆኗል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ እና በሌሎች ጉዳዮች ዙሪያ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት፤ንቅናቄው መጀመሩን ተከትሎ በክልሉ በርካታ ዞኖች ከተማ አስተዳደሮች የንቅናቄ መድረክ መካሄዳቸውን አስታውሰዋል፡፡ በዚህም ከዚህ ቀደም ለኢንዱስትሪ ምርታማነት እንቅፋት የሆኑ ችግሮች መቅረፍ የተቻለ ሲሆን መንግስትና ባለሀብቱ በቅርበት በጋራ እንዲሰሩ ምቹ እድል መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም በክልሉ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ ከማድረጉም በተጨማሪ ኢንቨስትመንቱ እንዲስፋፋ ማድረጉን ተናግረዋል። በተጨማሪም ንቅናቄው የስራ እድል እንዲሰፋ እንዲሁም ሌሎች ለክልሉ እድገት አስተዋጾ የሚያደርጉ ውጤቶች እንዲመዘገቡ አድርጓል ብለዋል። በበጀት አመቱ ብቻ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን ተከትሎ የተገኙትን ውጤቶች ርዕሰ መስተዳድሩ ለአብነት አንስተዋል፡፡ የገቢ ምርትን በመተካት በኩልም 324 ሚሊየን ዶላር የሚያወጣ ተኪ ምርት ማምረት መቻሉን አንስተዋል፡፡ እንዲሁም 50 ሺህ 772 የስራ እድል ለመፍጠር ታቅዶ ለ52 ሺህ 772 ዜጎች ስራ እድል መፍጠሩን ተናግረዋል። የመሰረተ ልማት ጥያቄ የሆኑት ለአምራቹ ዘርፍ አስፈላጊ የሆኑ የመብራት፣የውሃና ሌሎች ጥያቄዎች በፍጥነት መልስ ለመስጠት ጥረት እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ ምንም እንኳን በክልሉ አንዳንድ ቦታዎች ላይ የጸጥታ ችግር ቢኖርም የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴው እየጨመረ ባለሀብቱ በካፒታል መጠኑ እንዲያድግ እያደረገ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ክልሉ በትክክል ያለውን ጸጋ እንዲያስተዋውቅ በማገዝ ውጤታማ እያደረገው ይገኛል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በርካታ ትሩፋቶችን አስገኝቷል - ከንቲባ ከድር ጁሀር
Apr 30, 2025 40
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ለድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በርካታ ትሩፋቶችን ማስገኘቱን የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሀር ገለጹ። ኢትዮጵያን የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ ሀገራዊ የአስር ዓመት መሪ የልማት ዕቅድ ተዘጋጅቷል። እቅዱንም ለማሳካት ትኩረት ከተሰጣቸው ዘርፎች መካከል የአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ ዋነኛው ነው። ባለፉት አመታትም ይህንን የልማት ጉዞ በስኬት ለማጠናቀቅ የሚያስችሉ የተለያዩ ስትራቴጂዎች እና ፖሊሲዎች ተነድፈው ወደ ትግበራ ገብተዋል። ይህም የአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ ለሀገራዊ ኢኮኖሚ ዕድገት የሚያበረክተው አስተዋፅኦ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ይገኛል። እያጋጠሙ ያሉ ተግዳሮቶችን ለመፍታት በ2014 በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተጀምሯል። ይህም በሀገር አቀፍ ደረጃ የምርታማነት ንቅናቄዎች የተካሄዱ ሲሆን ስለኢንዱስትሪ ምርታማነት ሰፊ ግንዛቤ በሀገር አቀፍ ደረጃ እንዲፈጠር አድርጓል። ንቅናቄው ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በመተካት፣ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በጥራትና በብዛት ለማምረት እንዲሁም የግብርና እና ማዕድን ምርቶች ላይ ዕሴት ጨምሮ ለገበያ ለማቅረብ አዲስ ምዕራፍ ከፍቷል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሀር ንቅናቄው በድሬደዋ ከተማ በርካታ ትሩፋቶችን ማስገኘቱን ገልጸዋል። በተለይም ተኪ ምርቶችን በማምረት ላይ በርካታ ኢንዱስትሪዎች መሰማራታቸውን ገልጸው፤ ስራ አቁመው የነበሩ ኢንዱስትሪዎችም ወደ ምርት መመለሳቸውን ተናግረዋል። በሰራ ፈጠራ ረገድም በርካታ ወጣቶች በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በኢንዱስትሪዎች የስራ እድል እየተፈጠረላቸው መሆኑን ተናግረዋል። ከንቲባ ከድር ጁሀር አስተዳደሩ ለአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ምቹ ሁኔታን የመፍጠር ስራ እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በተለያየ ደረጃ የሚገኙ ኢንዱስትሪዎችን የማሳደግ ስራዎች መከናወናቸውን እና እነዚህም በራስ አቅም እየተሰሩ ያሉ ስራዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። በዚህም በተኪ ምርትና ኤክስፖርት ላይ ተሰማርተው የነበሩ ኢንዱስትሪዎች ከ5 ወደ 12 ከፍ ማለታቸውንም ጠቁመዋል።  
የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ በመጪው ቅዳሜ በይፋ ይከፈታል
Apr 30, 2025 68
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የ2017 ዓ-ም ኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ በመጪው ቅዳሜ በአዲስ አበባ በይፋ እንደሚከፈት የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አስታወቀ። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ኤክስፖውን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኢንዱስትሪዎች ያጋጥማቸው የነበሩ ችግሮች ደረጃ በደረጃ እንዲፈቱና የማምረት አቅማቸው እንዲጎለብት ማድረጉን አንስተዋል። ንቅናቄው የአገር ውስጥ ምርት አጠቃቀም ላይ ሰፊ ለውጦች መምጣታቸውን ገልጸዋል። 3ኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ በመጪው ቅዳሜ ሚያዝያ 25 ቀን 2017 ዓ-ም በይፋ እንደሚጀመር ገልጸው፥ የኢትዮጵያን ምርቶች ማስተዋወቅና ተጨማሪ የገበያ ዕድሎችን ማስፋት የኤክስፖው ዋና ዓላማ ነው ብለዋል። የገበያ ትስስሮችን መፍጠርና የምርት ጥራትን ለማሻሻልም ጉልህ ሚና ይኖረዋል ነው ያሉት። ፈጠራን ማበረታታትም አንዱ የኤክስፖው ዓላማ መሆኑን ጠቅሰው፤ የቴክኖሎጂ ሽግግርና የልምድ ልውውጥ መፍጠርም ዋነኛ ግቡ መሆኑን ተናግረዋል። በተለያዩ ክልሎች የተደረጉ ኤግዚቢሽንና ባዛሮች እንዲሁም የኢትዮጵያ ታምርት የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ የኢትዮጵያን ምርት በማስተዋወቅ በኩል ጉልህ ሚና ነበራቸው ብለዋል። በኤክስፖው 288 ኢንዱስትሪዎች የሚሳተፉ ሲሆን ከአራት ቢሊዮን ብር በላይ ግብይት ይፈፀማል ተብሎ ይጠበቃል። በአዲስ አለምአቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ለአምስት ቀናት የሚካሄደውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ከ120 ሺህ በላይ የአገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች እንደሚኖሩም በመግለጫው ተብራርቷል። በኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ምርቶችን ከማስተዋወቅ ባለፈ የተለያዩ የፓናል ውይይቶች፣የምርት ልማት ውድድሮች፣የተሻለ አፈፃፀም ላላቸው ኢንዱስትሪዎች የዕውቅና ፕሮግራም እና ሌሎችም መርሃ-ግብሮች ይከናወናሉ።
በክልሉ በዘንድሮው የመኸር ወቅት 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር ማሳ በዘር ለመሸፈን ታቅዷል
Apr 30, 2025 46
አሶሳ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ):- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በዘንድሮው የመኸር ወቅት 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር ማሳ በዘር ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ አቶ ባበክር ሃሊፋ ዛሬ በሰጡት መግለጫ፥በዘንድሮው የመኸር ወቅት 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር ማሳ በዘር ይሸፈናል። በአሁኑ ወቅት የማሳ ዝግጅት በሁሉም አካባቢዎች በመካሄድ ላይ መሆኑንም ኃላፊው ተናግረዋል። አርሶ አደሩም የኩታ ገጠም እርሻን ጥቅም በመረዳቱ ዘንድሮ በስፋት በዚሁ የግብርና ስነ-ዘዴ ለማልማት የሚያስችል የማሳ ዝግጅት እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ስራውን በማዘመን ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግ የሜካናይዜሽን ቴክኖሎጂ አቅርቦት ላይም በስፋት እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል። በግብርናው ዘርፍ ጥሩ አፈጻጸም በታየባቸው አካባቢዎች አርሶ አደሮች እና ባለሙያዎች የልምድ ልውውጥ ማድረጋቸውን አቶ ባበክር ተናግረዋል። የግብርና ስራውን ውጤታማ ለማድረግ በክልሉ የሚገኙ የልማት ጣቢያ ሰራተኞች በአዲሱ የግብርናና ገጠር ልማት ፖሊሲ፣ በግብርና ፍኖተ ካርታ እና ወቅታዊ የግብርና ስራዎች ላይ ስልጠና እየወሰዱ መሆናቸውንም አክለዋል። በዘንድሮው ዓመት ለክልሉ ከተመደበው 231 ሺህ ኩንታል ማዳበሪያ ውስጥ እስካሁን 100 ሺህ የሚጠጋ ኩንታል ወደ ክልሉ መግባቱን ጠቅሰዋል። ከዚህ ውስጥም 15 ሺህ ኩንታሉ መሰራጨቱን ጠቁመው፥ አርሶ አደሩ ግብዓቱን በወቅቱ ሊጠቀም እንደሚገባ አሳስበዋል። በሌላ በኩልም ከአራት ሺህ ኩንታል በላይ የምርጥ ዘር ወደ ክልሉ መግባቱን ተናግረዋል። አርሶ አደሩ ምንም አይነት የግብዓት እጥረት እንደማይገጥመው ያረጋገጡት ኃላፊው፥ ለመኸር እርሻ የጀመረውን ዝግጅት አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።
በዩኒቨርሲቲው 20 ኪሎ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት አቅም ያለው የባዮ ጋዝ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆነ
Apr 30, 2025 32
ወላይታ ሶዶ፤ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ ያስገነባውና 20 ኪሎ ዋት የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት አቅም ያለው የባዮ ጋዝ ፕሮጀክት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል። የባዮ ጋዝ ማብለያ ፕሮጀክቱ 300 ሜትር ኪዩብ የማብላላት አቅም እንዳለውም ተገልጿል። ፕሮጀክቱ ዩኒቨርሲቲው ከዚህ በፊት በኤሌክትሪክና በማገዶ ሲያከናውን የነበረውን የምግብ ማብሰል ሂደት ሙሉ በሙሉ በባዮጋዝ ሲስተም ለመተካት የሚያስችለው ነው። ባዮጋዙ ከተመረተ በኋላም ተረፈ ምርቱ የአፈር ማዳበሪያ ለማምረት እንደሚያስችል ተመላክቷል። በመርሃ ግብሩ ላይ በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኢነርጂ ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር)፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊ ኢንጂነር አክሊሉ አዳኝ እና ሌሎች የክልል አመራሮች፣የአጋር ድርጅቶች ተወካዮችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
የቴምር ምርትን ለማሳደግ የተጀመሩ ጥረቶችን ለማጠናከር ትኩረት ተሰጥቷል-ግብርና ሚኒስቴር
Apr 30, 2025 39
አይሳኢታ፤ሚያዝያ 22/2017 (ኢዜአ)፦የቴምር ምርትን ለማሳደግ የተጀመሩ ጥረቶችን ለማጠናከር ትኩረት መሰጠቱን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። በአፋር ክልል አይሳኢታና አፋምቦ ወረዳዎች ላይ እየተከናወነ ያለው የቴምር ልማት የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የስራ ኀላፊዎች ከሊፋ ዓለም ዓቀፍ የቴምር ልማትና ምርምር ተቋም ተወካዮች በተገኙበት የመስክ ምልከታ ተካሂዷል። ሚኒስቴሩ ከሊፋ ዓለም ዓቀፍ የቴምር ልማትና ምርምር ከተባለው የተባበሩት ዓረብ ኤሚሬቶች ተቋም ጋር በመሆን አይሳኢታና አፋምቦ ወረዳዎች ላይ ምርቱን ለማስፋት እና የምርምር ስራዎችን ለማከናወን የሚያስችሉ ተግባራት በማከናወን ላይ መሆኑም ተገልጿል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ኢፋ ሙለታ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፥በአፋር ክልል የቴምር ምርቶችን ለማሳደግ የተጀመሩ ጥረቶች አበረታች ሁኔታ ላይ ይገኛሉ። ጅምር ሥራዎቹን የአገሪቷ ሥነ ምህዳር በሚስማማባቸው ክልሎችና ዞኖች ለማስፈት የሚያስችሉ ተግባራት ይከናወናሉም ብለዋል። የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ድሪባ ገለቴ(ዶ/ር) በበኩላቸው፥ እንደ አገር በቴምር ላይ በተደረገ ምርምር ሁለት ዝርያዎች መውጣታቸውን ተናግረዋል። አስራ አራት የሚሆኑ ዝርያዎች ደግሞ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የዓለም ምግብና እርሻ ድርጅት ጋር በመሆን ለማውጣት እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። የቴምር ፍላጎት እንደ አገር በተለይም በፆም ወራት እየጨመረ የመጣ መሆኑን ጠቅሰው፥ በቀጣይ በስፋት ከተሰራ ከውጭ የሚገባውን ቴምር በአገር ውስጥ መተካት የሚቻል መሆኑን አስረድተዋል። በዋናነት አፋር ክልል አይሳኢታና አፋምቦ ወረዳዎች ለልማቱ ተመራጭ መሆናቸውን ገልጸው፥የሶማሌና ጋምቤላ ክልሎችም በዚህ ረገድ ምቹ ሥነምህዳር እንዳላቸው ገልፀዋል። የአፋር ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ ምክትል ሐላፊ አቶ ኡስማን መሐመድ እንዳሉት፥ በአይሳኢታና አፋምቦ ወረዳዎች አገር በቀል የሆነና 300 ዓመታትን ያስቆጠረ የቴምር ዝርያ መኖሩን አመልክተዋል። ይህም በምርምር በመታገዝ ምርታማነቱን በማሳደግ ተጠቃሚነትን ከማሳደግ አኳያ ሥራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዕለቱ የተገኙት የሠመራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት መሐመድ ኡስማን (ዶ/ር) በበኩላቸው፥ በምግብ ራስን ለመቻል ከሚደረጉት ጥረቶቾ አንዱ የቴምር ምርት ላይ የሚሰራውን ሥራ ማጠናከር ነው። ካለፈው ዓመት ጀምሮ ወደ ስራ ተገብቶ 2 ሺህ 500 ሄክታር ላይ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልፀው፥ በቀጣይ 10 ዓመታት ጊዜ ውስጥ አንድ ሚሊዮን የቴምር ዛፎችን መትከል ዓላማ ያደረገ ስራ ታቅዶ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የአፋር ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የመሬት አስተዳደር ቢሮ ኀላፊ አቶ ኡመር ኑሩ፣ የፌዴራልና የክልሉ ከፍተኛ የስራ ኀላፊዎች እንዲሁም የሠመራ ዩኒቨርሲቲ አመራሮች ተገተኝተዋል።
ለሕዳሴው ግድብ ግንባታ ቀሪ ሥራዎች የምናደርገውን ድጋፍ እናጠናክራለን-የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ነዋሪዎች
Apr 30, 2025 53
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዚያ 22/2017 (ኢዜአ):-ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ቀሪ ሥራዎች የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በደቡብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ነዋሪዎች ገለጹ። በክልሉ በበጀት ዓመቱ እስከ 600 ሚሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑም ተመላክቷል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ በክልሉ የወላይታ፣ የጌዴኦ እና የጋሞ ዞኖች ነዋሪዎች ለታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ቀሪ ሥራዎች የበኩላቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል። በወላይታ ዞን ሶዶ ከተማ ነዋሪ አቶ በቀለ ግምጃ እንደገለጹት ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያዊያንን ከዳር እስከ ዳር ያስተሳሰረ የአንድነት ምልክት ነው። የግድቡ ግንባታ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ድጋፍ ሲያደርጉ መቆየታቸውን ጠቅሰው፣ የግድቡን ግንባታ ቀሪ ሥራዎች ለማጠናቀቅም በሚደረገው ጥረት የሚጠበቅባቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል።   የጌዴኦ ዞን ዲላ ከተማ ነዋሪ ወጣት ተመስገን መኮንን በበኩሉ በኢትዮጵያውያን ትብብር ግንባታው ሲከናወን የቆየው የሕዳሴው ግድብ ወደ መጠናቀቅ በመድረሱ ደስታ እንደተሰማው ተናግሯል። የግድቡ መጠናቀቅ በቱሪዝምና በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ ለወጣቶች ሰፊ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ያለው ፋይዳ የጎላ መሆኑን ገልጸው፣ ግድቡ እኪጠናቀቅ ድረስ ድጋፋቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለመጪው ትውልድ "የአንድነት ውጤትን የምናሳይበት ቅርስ ነው" ያሉት ደግሞ በጋሞ ዞን የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ አዳነች ጩርቦ ናቸው። የሕዳሴው ግድብ ተጠናቆ ለአገልግሎት ሲበቃ የሃይል አቅርቦት ችግርን ይፈታል የሚል እምነት እንዳላቸውም ገልጸዋል። የግድቡ ግንባታ ሥራ ሙሉ ለሙሉ ተጠናቆ ለአገልግሎት እስኪበቃ ድረስ "የበኩሌን ድጋፍ አጠናክራለሁ" ሲሉም ተናግረዋል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ማስተባበሪያ ፕሮጀክት ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ዘርፉ አጥናፉ እንዳሉት በከልሉ በበጀት ዓመቱ ለግድቡ ግንባታ ቀሪ ሥራዎች ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ ለማሰባሰብ እየተሠራ ነው። በዚህም ባለፉት አራት ወራት በተደረገው ንቅናቄ ከ240 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ ለመሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል። የክልሉ ህዝብ ለሕዳሴው ግድብ በተለያየ መንገድ ድጋፍ በማድረግ አሻራውን ማኖሩን አስታውሰው፣ ይህም የህብረተሰቡን የቁጠባ ባህል ለማዳበር ማስቻሉን ተናግረዋል። የግድቡ ቀሪ ሥራ እንዲጠናቀቅ በሚደረገው ጥረት የክልሉን ህዝብ በማስተባበር ድጋፉ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል። በክልሉ ለታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ እስካሁን ከ670 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ መደረጉን ከማስተባበሪያ ጽህፈት ቤቱ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።  
የኮሪደር ልማት ስራው የመዲናይቱን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት በሚያሳድግ መልኩ ተጠናክሮ ይቀጥላል- ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 30, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦የኮሪደር ልማት ስራው ለዜጎች የዘመነች ከተማን ብሎም ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን በሚያሳድግ መልኩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ስብሰባውን አካሂዷል። በዚህም የምክር ቤቱ አባላት የተለያዩ ጥያቄዎችን ያነሱ ሲሆን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ለጥያቄዎቹ ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።   ከንቲባዋ የኮሪደር ልማት ስራን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ የለውጡ መንግስት መዲናዋን እንደስሟ ውብ እና ጽዱ የማድረግ ተግባር በስፋት እየተከናወነ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም በተገባው ቃል መሰረት አዲስ አበባን ለነዋሪዎቹ ምቹ እንድትሆን ብሎም አለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪነቷን ከፍ ለማድረግ የኮሪደር ልማት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም አንድ ከተማ ተወዳዳሪ ለመሆን ማሟላት ያለበት መስፈርቶች መኖራቸውን ተናግረዋል። ከእነዚህም መስፈርቶች መካከል የመሰረተ ልማት ጥያቄ መሆኑን ገልጸው፤ ለአብነትም የፍሳሽ አወጋገድ ስርአት፣ የመንገድ መሰረተ ልማት፣ የትራንስፖርት እና የአረንጓዴ ሽፋን ተጠቃሽ መሆናቸውን አብራርተዋል። ከዚህ አንጻር አዲስ አበባ ያለባትን ክፍተት ለመፍታት የተጀመረው የኮሪደር ልማት ስራ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎችን ያስገኘ መሆኑን አስረድተዋል። ህዝቡ ውብ፣ ጽዱ እና ለጤና ተስማሚ በሆነ አካባቢ እንዲኖር አቅም እና ልጆችን ለማሳደግም ምቹ መደላድልን የፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህም በተጨማሪ የከተማዋን የአረንጓዴ ልማት ሽፋን በከፍተኛ ደረጃ ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል። ከዚህም ባሻገር የኮሪደር ልማት ስራው የከተማዋን የመንገድ ሽፋን ወደ ላቀ ደረጃ ከፍ ለማድረግ የራሱን አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸው፤ ለዜጎችም በርካታ የስራ እድል የፈጠረ እንደሆነም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም