ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በየአካባቢው የሚገኙ ፀጋዎችን አሟጦ በመጠቀም ልማትን ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ይቀጥላል -ዶክተር አለሙ ስሜ
Mar 18, 2024 161
ሆሳዕና ፤መጋቢት 9/2016 (ኢዜአ)፦ በየአካባቢው የሚገኙ ፀጋዎችን አሟጦ በመጠቀም ልማትን ለማረጋገጥ እየተደረገ ያለው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትሩ ዶክተር አለሙ ስሜ ገለጹ። በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዶክተር አለሙ ስሜ የተመራ የፌዴራል የድጋፍና ክትትል ቡድን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በሀላባ ዞን ቁሊቶ ከተማ የተለያዩ የልማት ስራዎች ጎብኝቷል። ሚኒስትሩ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት በየአካባቢው የሚገኙና ያልተነኩ የልማት ጸጋዎችንና አቅሞችን በአግባቡ በመጠቀም የተጀመሩ ስራዎች ይጠናከራሉ ። በክልሉ የሀላባን ጨምሮ በሌሎች አካባቢዎች የተጀመሩ የልማት ስራዎችና የለውጥ እንቅስቃሴዎች አበረታች መሆናቸውን ጠቅሰው አሁንም የተጀመረው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል። በዛሬው ዕለት የተመለከቱት የሀላባና አጎራባች ዞኖች ሰላም ለመጠበቅና ለማረጋገጥ እየተሰራ የሚገኘው ስራ ትምህርት የሚወሰድበት መሆኑን ጠቅሰው የተጀመሩ የልማት ስራዎች ቀጣይነት እንዲኖራቸው የህብረተሰቡን ተሳትፎ ማደግ እንዳለበትም አክለዋል። በአርሶ አደሩ የሚመርቱ ምርቶችን በህብረት ስራ ማህበራት አማካኝነት በማቅረብ በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ ስለመሆኑም በመስክ ጉብኝታቸው ማረጋገጥ መቻላቸውን አብራርተዋል። የቁሊቶ ከተማን ውብና ማራኪ በማድረግ ረገድ አመራሩ ከማህበረሰቡ ጋር በቅርበት መስራት እንዳለበትም አመልክተዋል። የሀላባ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሀጂ ኑርዬ በበኩላቸው በዞኑ በኢንዱስትሪ፣ በግብርና፣ በሌማት ትሩፋትና በሌሎች ዘርፎች እየተከናወኑ የሚገኙ ተግባራት ከጊዜ ወደ ጊዜ ለውጥ እየተመዘገበባቸው ይገኛል ብለዋል። በእንስሳት ልማት 106 የተሻሻሉ የእንሰሳት ዝርያዎችን በማምጣት በወተትና በእንሰሳት ተዋጽኦ ልማት አበረታች ውጤት እየተመዘገበ መሆኑንም ጠቁመዋል። ጉብኝቱም በዞኑ እየተከናወኑ የሚገኙ የተለያየ ስራዎችን ጠንካራና ደካማ ጎን በመለየት ድጋፍ ለማግኘት የሚያስችል መሆኑንም ጠቅሰዋል። በዞኑ በሁሉም ዘርፍ ያሉ ሀብቶችን በአግባቡ በመጠቀም የነዋሪውን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። በመስክ ምልከታ መርሐ ግብሩ የፌዴራል፣ የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮች የተሳተፉ ሲሆን በነገው እለት በከንባታ ዞን የተለያየ አካባቢዎች የመስክ ምልከታ እንደሚደረግም ተገልጿል።
በሀዋሳና አካባቢዋ ያለውን ትልቅ አቅም የሚመጥን የልማት ስራ ማከናወን ይገባል - አቶ አህመድ ሽዴ
Mar 18, 2024 112
ሐዋሳ ፤መጋቢት 9/2016 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል ሀዋሳና አካባቢዋ ያለውን ትልቅ አቅም የሚመጥን የልማት ስራ ማከናወን እንደሚገባ የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ገለጹ ። በሚኒስትሩ የሚመራ የፌዴራል መንግስት የክትትልና ድጋፍ ሴፐርቪዥን ቡድን በሃዋሳ ከተማና በዙሪያዋ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል። ሚኒስትሩ ከገብኝቱ በኋላ እንደተናገሩት በሲዳማ ክልል ሀዋሳ ከተማና በዙሪያዋ ባሉ አካባቢዎች እየተከናወኑ ያሉ የልማት ተግባራት አበረታች ናቸው። ከተማዋ ካላት የኢኮኖሚ አቅም፣ በፌደራል መንግስቱ አማካይነት ከተገነቡ የተለያዩ መሰረተ ልማቶች አንጻር የአካባቢውን አቅም የሚመጥን የልማት ስራ ማከናወን እንደሚገባ ተናግረዋል። የከተማዋ ሃብት፣ ውበትና የእድገት ምንጭ የሆነውን የሀዋሳ ሃይቅ ዳርቻ ለማልማት የተከናወኑ ጅምር ስራዎች ቢኖሩም የሃይቅ ዳርቻ ልማቱን ማጠናከር ይገባል ብለዋል። የሀዋሳ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በአጫጭር፣ መካከለኛና በረዥም ጊዜ በሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎችን እንደሚያሰልጥን መመልከታቸውን ገልጸዋል። የአዳሬ ሆስፒታል ማስፋፊያና የአዳሪ ትምህርት ቤት ግንባታ በጤናና በትምህርት ዘርፍ የተጎበኙ ስራዎች ሲሆኑ ግንባታቸው ተጠናቆ በፍጥነት አገልግሎት መስጠት እንዲጀምሩ አመራሩ ተገቢውን ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚጠበቅበት አሳስበዋል። በከተማዋ የሚገኘው 'ሱፐር ኦቫ' የእንቁላል ፋብሪካ የመሳሰሉ ትላልቅ ፋብሪካዎችን ማበረታት የሀዋሳ ኢንደስትሪ ፓርክን ማገዝ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። ሚኒስትሩ አክለውም በሌማት ትሩፋትና በግብርና መስክ የተከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸውና የአካባቢውን ወጣት ወደ ዘርፉ ማሰማራት እንደሚገባ ገልጸዋል። የሀዋሳ ከተማ ምክትል ከንቲባ አቶ መኩሪያ መርሻዬ በበኩላቸው ለድጋፍና ክትትል ቡድን የስምንት ወራት አፈጻጻም ሪፖርት ቀርቦ መገምገሙን ገልጸዋል። ቡድኑ ከሪፖርቱ ባሻገር በተግባር እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችን ከትናንት ጀምሮ እየጎበኘ መሆኑን ገልጸው ጉብኝቱ ውጤታማ ተግባራትን ለማስቀጠልና ውስንነትን የታየባቸውን ለማረም የሚያግዝ ነው ብለዋል። ''ውጤት የታየባቸው የልማት ስራዎች ቢኖሩም ከተማዋ ካላት እምቅ አቅምና ሃብት አንጻር ሊሰሩ የሚገቡ በርካታ ተግባራት በመኖራቸው የበለጠ ለመስራት ተዘጋጅተናል" ብለዋል። እንደ ምክትል ከንቲባው ገለጻ በሌማት ትሩፋት ባለፉት ወራት ከ2 ሚሊየን በላይ የአንድ ቀን ጫጩቶች ማሰራጨታቸውን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ 12 ሺህ ዜጎች የስራ እድል ለመፍጠር ታቅዶ ባለፉት ስምንት ወራት ከ9 ሺህ በላይ ዜጎች የስራ እድል ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። የተጓተተው የአዳሬ ሆስፒታል ማስፋፊያና የአዳሪ ትምርት ቤት ግንባታ ስራዎችን በአጭር ጊዜ ለማጠናቀቅ ከተማ አስተዳደሩ በትኩረት እየሰራ መሆኑንም አንስተዋል። ጉብኝት ከተደረገባቸው መካከል 'ያሬድ የተለያዩ ማሽነሪዎችና መለዋወጫዎች ኢንጅነሪንግ' ባለቤትና መስራች አቶ ያሬድ እስጢፋኖስ የመንግስት አመራሮች ፋብሪካቸውን መጎብኘታቸው ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። በጉብኝቱ ስራ ሂደት የሚያያጋጥማቸውን የውጭ ምንዛሪ ችግር መቅረፍ የሚያስችላቸውን ምክረ ሃሳብ ማግኘታቸውንም ተናግረዋል። የቡድኑ አባላት የሀዋሳ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ፣ ኢንደስትሪ ፓርክ፣ የትምህርትና ጤና ተቋማትን ጨምሮ ትላልቅ የኢንቨስትመንስት ስራዎችም ጎብኝተዋል።
አፋር ክልል እየተሰሩ ያሉ የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ለማድረግ በትብብር መስራት ይገባል
Mar 18, 2024 113
ሰመራ ፤ መጋቢት 9/2016 (ኢዜአ)፡- አፋር ክልል ያለውን ዕምቅ አቅም ለመጠቀም እየተሰሩ ያሉ የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በትብብር መሠራት እንደሚገባ የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል ተናገሩ። በኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል የተመራ ቡድን በአፋር ክልል በዱብቲ፣ አፋምቦና አይሳኢታ ወረዳዎች እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን ተመልክተዋል። ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል ከጉብኝቱ በኋላ እንደገለጹት፤ በክልሉ አፋምቦ ወረዳ ከዚህ ቀደም ለልማት ያልዋሉ መሬቶች ለምተዋል። በተለይም በክልሉ ያለውን ሰፊ የተፈጥሮ ፀጋ ማልማት ከተቻለ ከፍተኛ ውጤት እንደሚገኝ በወረዳው የለማው የቴምር ተክል አመላካች ነው። በዚህም መሠረት በክልል ደረጃ ያለውን አቅም ከፌዴራል መንግስት ጋር በመናበብና በትብብር ልማቱን ይበልጥ ማሳደግ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጠውታል። ''በክልሉ የእንሰሳት መኖ ልማት ኤክስፖርት ሊደረግ የሚችል ዕምቅ አቅም ያለው መሆኑን ተረድተናል'' ያሉት የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ፤ በቀጣይም የዚህ ዓይነቱ ተግባር ለአርብቶ አደሩና ከፊል አርብቶ አደሩ የሚስፋፋበት ሁኔታ ትኩረት እንዲደረግበት ጠቁመዋል። ስለሆነም ክልሉ ያለውን ዕምቅ የተፈጥሮ አቅም በአግባቡ ማልማት እንዲችል ከፌዴራል መንግስት ድጋፍ እንደሚደረግም ተናግረዋል። ''እነዚህ የተመለከትናቸው ስራዎች ከተስፋ ሰጪነታቸው ጎን ለጎን ከፌዴራል እንዲሁም ከክልል መንግስታት የቴክኒክ ድጋፍ የሚያሻ ነው'' ብለዋል። የሱፐርቪዥን ቡድኑ በመሥክ ላይ ወጥቶ በክልሉ በተፈጥሮ ሐብት ጥበቃ ስራዎች፣ በስራ ዕድል ፈጠራ፣ ኑሮ ውድነት ከመቀነስ አኳያ ከኢንዱስትሪና ግብርና ስራዎች፣ ሌማት ትሩፋት እና ማህበራዊ አገልግሎቶች በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ በማረጋገጥ ክልሉ ያልተጠቀመባቸውን ዕምቅ አቅሞች በመለየት ድጋፍ ማድረግን ያለመ መሆኑን ተመላክቷል።
በየአካባቢው እየተከናወኑ ያሉ ተስፋ ሰጪ የልማት ስራዎች ውጤት እንዲያመጡ ሁሉም ሊረባረብ ይገባል -- አቶ ብናልፍ አንዷለም
Mar 18, 2024 110
አርባምንጭ፤ መጋቢት 9/2016 (ኢዜአ)፡- በየአካባቢው እየተከናወኑ ያሉ ተስፋ ሰጪ የልማት ስራዎች ውጤት እንዲያመጡ ሁሉም መረባረብ እንዳለበት የሰላም ሚኒስትሩ አቶ ብናልፍ አንዷለም ተናገሩ። በሰላም ሚኒስትር አቶ ብናልፍ አንዷለም የተመራ የፌደራል መንግስት የሱፐርቪዥን ቡድን በጋሞ ዞን ገረሴ ዙሪያ ወረዳ የልማት ስራዎችን ተመልክቷል። ቡድኑ በዛሬው ዕለት በዞኑ ገረሴ ዙሪያ ወረዳ የአረንጓዴ አሻራ ልማት እንዲሁም የሌማት ትሩፋት ስራዎችን ተመልክቷል። ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት የወረዳው ህዝብ በ2015 የአረንጓዴ አሻራ ልማት መርሃ ግብር ከ7 ነጥብ 8 ሚሊዮን በላይ ችግኞች መተከላቸውንና ለችግኞቹ እየተደረገ ያለው እንክብካቤም አድንቀዋል። ከሌማት ትሩፋት ጋር በተያያዘም የወተትና የከብት ማድለቢያ መንደር መለየቱን፣ የዕንቁላልና የማር መንደሮችም መደራጀታቸው አበረታች መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በወረዳው 31 የወተት፣ 35 የዶሮ፣ 31 የማርና 12 የከብት ማድለብ መንደር እንዳለ መረዳታቸውን ገልጸው ይህም ለወጣቶች ስራ ዕድል ማግኛ እንደሆነም ጠቅሰዋል። እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ በወረዳው እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች መልካም ጅማሮና ተስፋ ሰጪ ናቸው ብለዋል። በአገር ደረጃም የተያዙ የልማት ግቦች እንዲሳኩ በየአካባቢው እየተከናወኑ ያሉ ተስፋ ሰጪ የልማት ስራዎች እንዲቀጥሉ ሁሉም መረባረብ አለበት ብለዋል። የገረሴ ዙሪያ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ካሳሁን ካማ፣ ወረዳው በአካባቢው ዘላቂ ሰላም ከማረጋገጥ አኳያ ጠንካራ ማህበራዊ ሀብት መኖሩን አስረድተዋል። በዚህም ግጭትን አስቀድሞ በመከላከል እና ሲፈጠርም በባህላዊ መንገድ በመፍታት የህብረተሰቡን ሰላምና ፀጥታ የመጠበቅ ተግባር እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በበጀት ዓመቱ በወረዳው 2 ሺህ 256 የስራ አጥ ወጣቶች ልየታ የተደረገ ሲሆን በ6 ወራት ለ987 ወጣቶች የስራ ዕድል መፈጠሩን ገልፀዋል። በወረዳው በትምህርት ቤቶች የሚስተዋለውን የትምህርት ቁሳቁስ እጥረት እና የክፍል ጥበት ችግር ለመቅረፍ ከህብረተሰቡ በተገኘ ከ11 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር ድጋፍ በማሰባሰብ የተለያዩ ስራዎች መሰራታቸውን ገልጸዋል። የሱፐርቪዥን ቡድኑ አባላት በገረሴ ከተማ በጎ ፍቃደኛ ወጣቶች ለአንዲት የአካል ጉዳተኛ የገነቡትን ቤት የጎበኙ ሲሆን የቡድኑ አባላት ለአካል ጉዳተኛዋ መቋቋሚያ የሚሆን የ20 ሺህ ብር ድጋፍም አድርገዋል። ቡድኑ በነገው ዕለት በአርባ ምንጭ ከተማ የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን በመመልከት አጠቃላይ ግብረ መልስ ለጋሞ ዞን አስተዳደር አካላት እንደሚሰጥ ይጠበቃል።
በደቡብ ወሎ ዞን በበጋ መስኖ ስንዴና በሌማት ቱሩፋት መርሃ ግብር የተከናወኑ ተግባራት አበረታች ናቸው - ዶክተር ለገሰ ቱሉ
Mar 18, 2024 173
ደሴ ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን በበጋ መስኖ ስንዴና በሌማት ቱሩፋት መርሃ ግብር የተከናወኑ ተግባራት በአካባቢው የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያግዙ መሆናቸውን የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዶክተር ለገሰ ቱሉ ገለፁ። በዶክተር ለገሰ ቱሉ የተመራ የፌደራል መንግስት የድጋፍና ክትትል ቡድን በደቡብ ወሎ ዞን ደሴ ዙሪያና ተሁለደሬ ወረዳዎች የበጋ ወቅት ስራዎችና የሌማት ቱርፋት ተግባራትን ተመልክቷል። ሚኒስትሩ ዶክተር ለገሰ ቱሉ በጉብኝቱ ወቅት እንዳሉት ኢኮኖሚውን በማነቃቃት ምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው። በደቡብ ወሎም የበጋ መስኖ ስንዴን የማልማትና በሌማት ትሩፋትም አስፈላጊ የሆኑ ምርቶችን በማምረት ለህብረተሰቡ ተደራሽ እየተደረገ መሆኑን መመልከታቸውን ገልጸዋል። የስራ እድል ፈጠራውን ከሌማት ቱርፋት ጋር በማስተሳሰር በወተት፣ በእንቁላል፣ በማርና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች በማምረት የገበያ ክፍተቱን ለመሙላት እየተሰራ ያለው ስራ አበረታች ነው ብለዋል። ይህም የተቀረጸው የአገር በቀል ኢኮኖሚ ውጤታማነት ማረጋገጫ መሆኑን በዞኑ እየተከናወነ ያለው ስራ ማሳያ መሆኑን መመልከታቸውን ተናግረዋል። የፌዴራል መንግሥትም በየጊዜው የድጋፍ ቡድን በመላክ ድጋፍና ክትትል በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ጠቁመው ድጋፉ በቀጣይ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮንን በበኩላቸው በዞኑ በበጋ መስኖ ስንዴ ከለማው 26 ሺህ ሄክታር መሬት ከ700 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል ብለዋል። በሌማት ቱርፋት መርሃ ግብርም ሁሉም የዞኑ ነዋሪ በአካባቢው አትክልትና ፍራፍሬ፣ ዶሮና የመሳሰሉትን በማልማትና በማርባት በንቃት እንዲሳተፍ መደረጉን ገልጸዋል። በዶሮ እርባታ በተፈጠረልን የስራ እድል ለመለወጥ እየሰራን ነው ያለችው ደግሞ በደሴ ዙሪያ ወረዳ የ015 ቀበሌ ነዋሪ ወጣት ሀቢባ ኢብራሂም ናት። ዘንድሮ 61 ሆነው በመደራጀት 1 ሺህ 100 እንቁላል ጣይ ዶሮዎችን ማርባት መጀመራቸውን ጠቁማ በቀን ከ600 በላይ እንቁላል ማግኘት መጀመራቸውን ጠቁማለች። የፌደራል መንግስት የድጋፍ ቡድኑ በሐይቅ ከተማ በገበታ ለትውልድ የሚለማውን የሎጎ ሐይቅንም ጎብኝተዋል።
በመዲናዋ የሚገኙ የህብረት ስራ ማህበራትን በቴክኖሎጂ በመደገፍ ውጤታማ ለማድረግ የሚያስችል የሪፎርም ስራ ይከናወናል- ጃንጥራር አባይ
Mar 18, 2024 61
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ የሚገኙ የህብረት ስራ ማህበራትን በቴክኖሎጂ በመደገፍ ውጤታማ ለማድረግ የሚያስችል የሪፎርም ስራ እንደሚከናወን የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ ገለጹ። የመዲናዋ የሕብረት ሥራ ኮሚሽን "የማኅበራትን ኃብትና ንብረት ከብክነት በመጠበቅ የአባላቱንና የኅብረተሰቡን ተጠቃሚነትን እናረጋግጥ"በሚል መሪ ኃሳብ ሲያካሒድ የነበረውን መርሃ ግብር አጠናቋል። በመርሃ ግብሩ ማጠናቀቂያ ላይ የከተማ አስተዳዳሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣የክፍለ ከተሞችና ወረዳዎች የህብረት ስራ ማህበራት ተወካዮች ተገኝተው በሪፎርሙ ላይ ውይይት አድርገዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ፤ሕብረት ስራ ማሕበራት የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችላቸው ሪፎርም እየተዘጋጀ ነው። ሪፎርሙ የማኅበራቱን የአሠራር ሥርዓት የሚያዘምን እንዲሁም ጠንካራ አደረጃጀት በመፍጠር የቁጥጥርና የክትትል ሥራን ለማጠናከር የሚያስችል እንደሆነ ነው የጠቆሙት። በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራትና የአሠራር ሥርዓቱን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እንደሚያግዝም ነው ያብራሩት። በአሁኑ ወቅት ከተማ አስተዳደሩ የኅብረት ሥራ ማኅበራት አሠራራቸውን በማሻሻል ምርቶችን በስፋት ወደ ገበያ እንዲያቀርቡ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል ። በማህበራቱ ላይ ጠንካራ የክትትልና ቁጥጥር ስራ እንደሚከናወንም ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አበባ ህብረት ስራ ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ልዕልት ግደይ በበኩላቸው፤ኮሚሽኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የህብረት ስራ ማህበራትና ተገልጋዩን ያካተተ ጥናት በማካሔድ የሪፎርም ስራ እያከናወነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ሪፎርሙ የተዘጋጀበት ዋና ዓላማ ጠንካራ ተቋም በመገንባት ጥራት ያለው አገልግሎት ለመስጠት እንዲቻል ነው ብለዋል። ሪፎርሙን ለመተግበርም ከህብረት ስራ ማህበራትና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር የተለያዩ ተግባራትን እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። ከዚህ ውስጥም በዘርፉ ስራ ላይ የሚውል ቴክኖሎጂን የማበልፀግና አሳሪ የሆኑ መመሪያዎችን የማሻሻል ስራም አንዱ መሆኑን አመልክተዋል። የየካ ክፍለ ከተማ የወረዳ አራት የሸማች ሕብረት ስራ ማህበራት አመራር ኮሚቴ ሰብሳቢ ዳኘ ከበደ እና አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ የቱሉ ዲምቱ ሸማቾች ማህበር ስራ አሲኪያጅ ወይዘሮ ሰሀራ ንጉሴ፤ ሪፎርሙ በቴክኖሎጂ የተደገፈ አሰራርን በመተግበር የማህበራቱ አሰራር ላይ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለማስተካከል እንደሚያግዝ ተናግረዋል፡፡ በመዲናዋ ከ9 ሺህ 800 በላይ ህብረት ስራ ማህበራት እንደሚገኙ የኮሚሽኑ መረጃ ያሳያል።
የኢትዮጵያ የሸማቾች መብት ጥበቃ ማህበራት ጥምረት ተመሰረተ
Mar 18, 2024 53
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በሸማቾች መብት ላይ ትኩረቱን አድርጎ የሚሰራ የኢትዮጵያ የሸማቾች መብት ጥበቃ ማህበራት ጥምረት ተመስርቷል፡፡ ጥምረቱ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴዔታ አቶ እንዳለው መኮንን፣ የንግዱ ዘርፍ ባለድርሻ አካለትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በዛሬው እለት በአዲስ አበባ ከተማ ተመስርቷል፡፡ የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴዔታ አቶ እንዳለው በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ ሸማቾች በግብይት ስርዓቱ ላይ ትልቁን ድርሻ ይዘው ቢገኙም መብቶቻቸው ግን እየተከበረ አይደለም፡፡ በከፈሉት ዋጋ ልክ ደህንነቱ እና ጥራቱ የተጠበቀ ተመጣጣኝ ምርትና አገልግሎት አያገኙም ነው ያሉት፡፡ ይህ ደግሞ የራሳቸውን አደረጃጀት ፈጥረው ለመብቶቻቸው በጋራ መታገል ባለመቻላቸው የመጣ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ ሽማቾች መንግስት በአዋጅ ያስቀመጠላቸውን መብት በአግባቡ ለመጠቀም መደራጀት እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡ ለዚህም ሚኒስቴሩ በቀጥታ የሸማቾች መብት እንዲከበር ከሚሰራቸው ስራዎች ጎን ለጎን ጠንካራ አደረጃጀት እንዲፈጥሩ የተለያዩ ጥረቶችን ሲያደርግ መቆየቱን አመላክተዋል፡፡ በዚህም በዛሬው እለት ክልሎችንና ሁለቱን ከተማ አስተዳደሮች ጋር በመሆን በኢትዮጵያ የመጀመሪያ የሆነው የኢትዮጵያ የሸማቾች መብት ጥበቃ ማህበራት ጥምረት እንዲመሰረት ተደርጓል ብለዋል፡፡ ዛሬ የተመሰረተው ጥምረት በአገር አቀፍ ደረጃ ሸማቾች በህግ የተሰጣቸውን መብት እንዲያውቁ እና በግብይት ሒደት የሚያጋጥማቸውን የመብት ጥሰቶች በጋራ እንዲታገሉ የሚያግዝ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ጥምረቱ ይህን ለማድረግ ከፍተኛ ሃላፊነት የተጣለበት መሆኑን በመገንዘብ ለተግባራዊነቱ የሚጠበቅበትን እንዲወጣ አሳስበዋል፡፡ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱም ጥምረቱ የሚያከናውናቸው ተግባራት እውን እንዲሆኑ ከጎኑ እንደሚቆም አረጋግጠዋል፡፡ የኢትዮጵያ የሸማቾች መብት ጥበቃ ማህበራት ጥምረት በፕሬዝዳንት እንዲመሩ የተመረጡት እንግዳ አስፋው በበኩላቸው፣ የሸማቾች መብት በአዋጅ ያለ ቢሆንም እስካሁን ድረስ ግን ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ አለመደረጉን ገልጸዋል፡፡ ይህም ሸማቾች ስለመብቶቻቸው በቂ ግንዛቤ ባለመያዛቸውና መብቶቻቸው ሲጣሱም ከለላ የሚሆንላቸው ማህበራት ባለማቋቋማቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ዛሬ የተመሰረተው ጥምረት በተለይ ሽማቹን ስለመብቱ ግንዛቤ የመፍጠርና መብቶች ተጥሰው ሲገኙም ከሚመለከተው አካል ጋር በመሆን የህግ ከለላ እንዲያገኙ ያደርጋል ብለዋል፡፡ የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር በዛሬው እለት ዓለም አቀፍ የሸማቾች ቀንን "በህብር መብታችንን እናስከብር" በሚል መሪ ሃሳብ አክብሯል።
በግብርና ፣በትምህርት ፣በጤናና በሌሎች ዘርፎች የተገኙ ውጤቶች የሚበረታቱ ናቸው - ኢንጂነር አይሻ መሀመድ
Mar 18, 2024 66
አዲስ አበባ፤መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦በግብርና ፣በትምህርት ፣በጤና እና በሌሎች ዘርፎች የተሰሩት ስራዎች የሚበረታቱና ሊሰፉም እንደሚገባ የመስኖ እና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሃመድ ገለጹ። በኢንጂነር አይሻ መሃመድ የተመራ የፌደራል የድጋፍ እና ክትትል ቡድን በአሶሳ ዞን ባምባሲ ወረዳና በባምባሲ ከተማ አስተዳደር የመስክ ልማት ስራዎችን ጎብኝቷል። በጉብኝቱም ሚኒስትሯና የክትትል ቡድኑ የበጋ መስኖ ስንዴ ፣የዶሮ እርባታ ፣ አፈርና ውሃ እቀባ ስራዎችና በሌሎች ዘርፎች የተከናወኑት የልማት ስራዎችን መመልከት ችለዋል፡፡ በዚህ ጊዜም ኢንጂነር አይሻ በግብርና ፣በትምህርት ፣በጤና እና በሌሎች ዘርፎች የተሰሩትን ስራዎች የሚበረታቱ መሆናቸውን ገልጸው በቀጣይ በሁሉም አካባቢ ሊሰፉ እንደሚገባ አሳስበዋል። ወረዳውና የከተማ አስተዳደሩ በአካባቢው የሚገኙ ጸጋና ምቹ ሁኔታዎችን ተጠቅሞ ከዚህ በላይ ማልማት እንደሚኖርበትም ገልጸዋል። የክትትልና ሱፐርቪዥን ቡድኑ አባላት በመስክ ምልከታው በሁሉም ዘርፍ የታዩት የልማት ስራዎች በተዋረድ ያለው የመንግስትና የፓርቲው ክትትልና ቅንጅታዊ የስራ ውጤት መሆኑን ገልጸው በቀጣይም ክፍተቶችን በማረም በሁሉም ዘርፍ የበለጠ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል አብራርተዋል። በመስክ ምልከታው የፌዴራል የሱፐርቪዥን ቡድንን ጨምሮ ፣የክልል ፣የዞን እና የወረዳው አመራሮች መሳተፋቸውን ከብልጽግና ፓርቲ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በባንኩ የደንበኞች የግል አካውንት ላይ የደረሰ ምንም አይነት ጉዳት የለም - የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
Mar 18, 2024 132
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፡- በባንኩ የደንበኞች የግል አካውንት ላይ የደረሰ ምንም አይነት ጉዳት አለመኖሩን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አስታወቀ። ባንኩ ሰሞኑን አጋጥሞት የነበረውን የአገልግሎት መቋረጥ ችግር አስመልክቶ መግለጫ ሰጥቷል። በዚህም በባንኩ የደንበኞች የግል አካውንት ላይ የደረሰ ምንም አይነት ጉዳት የለም ሲሉ የባንኩ ፕሬዝዳንት አቶ አቤ ሳኖ በመግለጫቸው ይፋ አድርገዋል። ባንኩ የውስጥ አሰራሩን ለማዘመን ሲያደርግ በነበረው እንቅስቃሴ አርብ መጋቢት 6 ለሊቱን በተፈጠረ ስህተት ምክንያት ጤናማ ያልሆነ የገንዘብ እንቅስቃሴ እንደነበረ መጠቆማቸውን የኢቢሲ ዘገባ ያመላክታል። ፕሬዝዳንቱ በመግለጫቸው እንደገለጹት የተፈጠረው ክስተት ከሳይበር ጥቃት ጋር የተያያዘ አይደለም። አርብ ለሊት ብቻ ከ490 ሺህ በላይ የገንዘብ ልውውጥ እንደነበር የተገለፀ ሲሆን ይህ የገንዘብ ልውውጥ ጤናማ የሆነውንም እንደሚጨምር ተጠቁሟል። ገንዘብ በተለያየ መንገድ ጤናማ ባልሆነ መልኩ ከባንኩ በማውጣት ላይ በዋናነት የተሳተፉት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ናቸው ያሉት ፕሬዝዳንቱ አብዛኛው ተማሪዎች በባንኩ በተደረገላቸው ጥሪ መሰረት የወሰዱትን ገንዘብ እየመለሱ መሆኑ ገልፀዋል። የባንኩን ጥሪ ተቀብለው ገንዘቡን ተመላሽ ላደረጉ ተማሪዎች ባንኩ ምንም አይነት ክስ እንደማይመሰርትም ማስታወቃቸውን በዘገባው ተመላክቷል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በተደጋጋሚ በሀገራት በሚደገፉ ትልልቅ ተቋማት ጭምር የሳይበር ጥቃቶች ሙከራዎች ቢያጋጥሙትም አስተማማኝ የሳይበር ደህንነት ያለው ተቋም በመሆኑ ሁሉንም ሲያከሽፍ እንደቆየ ነው ፕሬዝዳንቱ የገለፁት። የደረሰው ጉዳት ከባንኩ አጠቃላይ ሀብት አንፃር በጣም አነስተኛ ነው ያሉት ፕሬዝዳንቱ የደንበኞች የግል አካውንት ላይ የደረሰ ምንም አይነት ጉዳት ባለመኖሩ ደንበኞች ምንም አይነት ስጋት ሊገባቸው እንደማይገባ የባንኩ ፕሬዝዳንት መግለጻቸውም ተጠቁሟል።
በሰብል ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ተባዮችና ሌሎችንም ቀድሞ ለመከላከል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑ ተገለጸ
Mar 18, 2024 108
አዳማ፤መጋቢት 9/2016 (ኢዜአ)፦በሰብል ምርታማነት ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ተባዮችንና ሌሎች ችግሮችን ቀድሞ ለመከላከል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑ ተገለጸ። የተቀናጀ ፀረ ተባይና ተምች መከላከያና ቁጥጥር ስርዓት ላይ ያተኮረ መድረክ በአዳማ ተካሄዷል። በግብርና ሚኒስቴር የዕፅዋት ጥበቃ መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ በላይነህ ንጉሴ በወቅቱ እንደገለጹት የብርዕና የአገዳ ሰብሎች በተባዮችና በተለያዩ ችግሮች እንዳይጎዱ ለቅድመ መከላከል ስራው ትኩረት ተደርጓል። በብርዕና የአገዳ ሰብሎች እንዲሁም በአትክልትና ፍራፍሬ ሰብሎች ላይ ሊከሰቱ የሚችሉ እንደ የአሜሪካን መጤ ተምች፣ የስንዴ ራስ አድርቅ፣ የበረሃ አንበጣ፣ ቢጫ ዋግ፣ ግሪሳ ወፍ የመሳሰሉትን ቀድሞ ለመከላከል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ነው የገለጹት። በተለይም ከማሳ ዝግጅት ጀምሮ እስከ ቡቃያ ድረስ በኬሚካል ታግዞ ከሚደረገው የመከላከል ስራ ጎን ለጎን በባህላዊ መንገድ ለመከላከልም እንደሚሰራ ተናግረዋል። በተለይም የተምች አሰሳና የኬሚካል አጠቃቀም ላይ ሙያተኞችና የግብርና ዘርፍ የስራ ሃላፊዎች በዕውቀትና በሙያ የተደገፈ ክህሎት እንዲቀስሙ የአቅም ግንባታ ስልጠና እየተሰጠ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህም ከፌዴራል ጀምሮ እስከ ወረዳና ቀበሌ ድረስ ያሉ የዘርፉ ሙያተኞችን እውቀትና ክህሎት ለማሳደግ ተከታታይ ስራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ፀረ ተባይና ፀረ አረም ኬሚካል በአግባቡ ጥቅም ላይ መዋል ለምርታማነት መሻሻል ጉልህ ድርሻ እንዳለው የተናገሩት ደግሞ በዓለም ምግብ ፕሮግራም ድርጅት የነፍሳትና የተቀናጀ የፀረ ሰብል ተባይ ባለሙያ ዶክተር ባየህ ሙላቱ ናቸው። በአንዳንድ ቦታዎች ላይ ከአጠቃቀም ጉድለት የተነሳ ሰብሉ ላይ ጉዳት እየደረሰ መሆኑን የገለጹት ባለሙያው የተቀናጀ አመራረትና የፀረ ተባይ ቁጥጥር ስርዓት በመዘርጋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ ይገባል ነው ያሉት። ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል ከኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን የመጡት አቶ አንተነህ ፈዬራ፣ ውይይቱ በአጠቃቀም ወቅት የነበረብን የዕውቀትና የክህሎት ክፍተት የሚሞላ ከመሆኑም ባለፈ የቅድመ መከላከል ስራ ላይ ትኩረት አድርገን እንድንሰራ ልምድ ያገኘንበት ነው ብለዋል። በተለይም የቦሎቄና በቆሎ ቢጫ ዋግ፣ የስንዴ ራስ አድርቅ እንዲሁም ግንድና ቅጠል በሊታ ተምቾች መከላከል ላይ ከማሳ ዝግጅቱ ጀምሮ እስከ ዘርና አረም ድረስ የመከላከል ሂደቱ ላይ ግንዛቤ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። በውይይቱ ላይ ከምርምር ተቋማት፣ ከዩኒቨርሲቲዎች፣ ከዓለም ምግብ ፕሮግራም፣ ከበረሃ አንበጣ መከላከያ ማዕከል እንዲሁም ከግብርና ሚኒስቴርና ከክልል ግብርና ቢሮ ተወካዮች ተሳትፈውበታል።
የአየር መንገዱን የደንበኞች አገልግሎት ይበልጥ ምቹና ቀልጣፋ ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Mar 18, 2024 109
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ የአየር መንገዱን የደንበኞች አገልግሎት ይበልጥ ምቹና ቀልጣፋ ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው፤ በአየር መንገዱ እየተከናወኑ ያሉ በርከት ያሉ ስራዎችን በተመለከተ መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም በተያዘው በጀት ዓመት በስድስት አዳዲስ ዓለም አቀፍ መዳረሻዎች ለመብረር አቅዶ እስካሁን ሶስቱን ማሳካቱን ጠቅሰዋል። በአውሮፕላን ግዥም ስምንት አውሮፕላኖችን ለመግዛት ታቅዶ እስካሁን የስድስት አውሮፕላን ግዥ መሳካቱን ገልጸዋል። በቀጣይነትም የ124 አውሮፕላኖች የግዥ ትእዛዝ መኖሩን ጠቁመዋል። ከመሰረተ ልማት አንፃርም የኢ-ኮሜርስ ፋሲሊቲ፣ የሃይል አቅርቦት ሰብስቴሽን እንዲሁም የሀገር ውስጥ በረራ ተርሚናል ግንባታ ተጠናቆ ስራ መጀመሩን ገልጸዋል። በግንባታው ዘርፍ የተርሚናል ሁለት ማስፋፊያ መደረጉን አንስተው አሁን ላይ ተጨማሪ የማስፋፊያ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ተናግረዋል። ከደንበኞች አገልግሎት ጋር በተያያዘ በተመዘገበው ስኬት አየር መንገዱ የተለያዩ አለም አቀፍ እውቅና እና ሽልማቶችን ማግኘቱንም ጠቅሰዋል። በአገልግሎት አሰጣጡ የሚስተዋሉ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት የሚያስችሉ አዳዲስ አሰራሮች ተግባራዊ ይደረጋሉ ብለዋል። የአየር መንገዱን የደንበኞች አገልግሎት ይበልጥ ምቹና ቀልጣፋ ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑንም አረጋግጠዋል። አየር መንገዱ ለደንበኞች አገልግሎት ሁሉንም ጥረት እንደሚያደርግ ገልጸው ቅሬታዎች ሲኖሩ የሚስተናገዱበት ስርዓት መዘርጋቱን አንስተዋል፡፡ የሚቀርቡ ቅሬታዎችን ተከትሎ ተገቢውን ምርመራ በማድረግ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድም አንስተዋል፡፡ የአየር መንገዱን የደንበኞች አገልግሎት ይበልጥ ምቹና ቀልጣፋ ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ነው የተናገሩት፡፡ በቀጣይም በቢሾፍቱ ከተማ በዓመት 100 ሚሊዮን መንገደኞችን ማስተናገድ የሚያስችልና 300 አውሮፕላኖችን የሚያቆም አዲስ ሚጋ አውሮፕላን ማረፊያ እንደሚገነባም ጠቁመዋል፡፡ ይህም አሁን ያለውን ተርሚናል በአራት እጥፍ የሚያሳድግ መሆኑን ገልጸዋል።
በሐረሪ ክልል ከ"መደመር ትውልድ" መጽሃፍ ሽያጭ በተገኘ ገቢ የሚገነባው የኢኮ ፓርክ ግንባታው በመፋጠን ላይ ነው
Mar 18, 2024 62
ሐረር፤ መጋቢት 09/2016 (ኢዜአ)፡-በሐረሪ ክልል ከ''መደመር ትውልድ' መጽሐፍ ሽያጭ በተገኘ ገቢ የሚገነባው የ"ኢኮ ፓርክ" ግንባታ በመፋጠን ላይ መሆኑን የክልሉ ባህል፣ ቱሪዝምና ቅርስ ቢሮ አስታወቀ። የፌዴራል መንግሥት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በክልሉ ከ''መደመር ትውልድ'' መጽሐፍ ሽያጭ በተገኘ ገቢ እየተገነባ የሚገኘውን የ"ኢኮ ፓርክን" የግንባታ ሂደት ተመልክተዋል። የክልሉ ባህል፣ ቱሪዝምና ቅርስ ቢሮ ሃላፊ አቶ ተወለዳ አብዶሽ በወቅቱ እንደገለፁት ከ ''መደመር ትውልድ'' መጽሐፍ ሽያጭ በተገኘው ገቢና የክልሉ መንግስት ባደረገው ድጋፍ 162 ሚሊዮን ብር በክልሉ በተለምዶ "ሴላት "በሚባለው አካባቢ ኢኮ ፓርኩ እየተገነባ ነው። ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ( ዶ/ር) በተሰጠ አቅጣጫ በ24 ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የሚያርፈው የኢኮ ፓርኩ የግንባታ ስራው በመፋጠን ላይ ነው ብለዋል። አጠቃላይ የግንባታ ስራው በአሁኑ ወቅት 65 በመቶ መጠናቀቁን ጠቁመው "ኢኮ ፓርኩ" ከጅብ የማብላት ትርዒት ባለፈ የተለያዩ የቱሪስት መስህቦችን በሚያቅፍ መልኩ እየተገነባ እንደሆነ አመልክተዋል። ኢኮ ፓርኩ ለቱሪስቶች ምቹና ቀንም ሆነ ምሽት አገልግሎት የሚሰጥ ሆኖ የክልሉን ባህልና ቅርሶች በያዘ መልኩ እየተገነባ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ፓርኩ ከጅብ ማብላት ትርዒት ሥፍራ በተጨማሪ አምስቱን በሮች፣ ጋለሪ፣ ሙዚዬም፣ ዘመናዊና ባህላዊ ሬስቶራንት፣ ቤተ መጻህፍት፣ የህጻናት መጫወቻና ኮንፍረንስ ማዕከል እንደሚያካተት አስታውቀዋል። ኢኮ ፓርኩ የሐረሪ ክልል ባህልና እሴትን የሚያሳዩ የዕደ ጥበብ ውጤቶች የሚመረቱበት፣ የሚተዋወቁበትና የሚሸጡበት መሆኑንም አስረድተዋል። የፓርኩ ግንባታ በተያዘለት ቀነ ገደብ ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በጉብኝቱ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈርያት ካሚልና የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪን ጨምሮ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል። በሐረሪ ክልል ከ"መደመር ትውልድ" መጽሃፍ ሽያጭ 70 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱ ይታወሳል።
የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ቡድን በደቡብ ወሎ ዞን የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን እየተመለከተ ነው
Mar 18, 2024 87
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዶክተር ለገሰ ቱሉ የተመራ የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ቡድን በደቡብ ወሎ ዞን የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን እየተመለከተ ይገኛል። መንግስት ባስቀመጠው አቅጣጫ በመላ ሀገሪቱ ሁሉም አካባቢዎች የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች የመስክ ምልከታና ድጋፋዊ ክትትል በፌዴራል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እየተደረገ ይገኛል። መንግስት በሀገር ደረጃ በሁሉም ክልሎች ያሉ ሐብቶችና ጸጋዎችን በአግባቡ ለመጠቀም እንዲቻል፣ የሚነሱ ቅሬታዎችንም ከኀብረተሰቡ ጋር ተቀራርቦ ለመፍታት በርካታ ሥራዎችን በማከናወን ላይ ሲሆን የድጋፋዊ ሱፐርቪዥን መርሃ ግብሩም የዚህ ተግባር አንድ አካል መሆኑ ተጠቁሟል። በዶክተር ለገሰ ቱሉ የተመራው የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ቡድንም በደቡብ ወሎ ዞን የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን ምልከታ በማድረግ ላይ ይገኛል። ምልከታቸው በዞኑ ውስጥ የተከናወኑ የበጋ መስኖ ሥንዴ ልማት፣ የተፈጥሮ ሐብት ልማትና ጥበቃ ሥራ፣ የሌማት ትሩፋት፣ የሥራ ዕድል ፈጠራና ሌሎች የልማት ሥራዎችን ያካተተ መሆኑን ከአማራ ኮሙኒኬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
ህዝብን በልማት ተጠቃሚ ለማድረግ የሚካሄዱ ተግባራት እንዲሳኩ በትብብር መስራት ያስፈልጋል-ዶክተር ፍጹም አሰፋ
Mar 18, 2024 197
ሚዛን አማን ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ ህዝብን በልማት ተጠቃሚ ለማድረግ የሚካሄዱ ተግባራት እንዲሳኩ በትብብር መስራትን ማጠናከር ያስፈልጋል ሲሉ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዶክተር ፍጹም አሰፋ አስገነዘቡ። በፕላንና ልማት ሚኒስትር ዶክተር ፍጹም አሰፋ የተመራ የሱፐርቪዥን ቡድን በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የተለያዩ የልማት ሥራዎችን እየተመለከተ ነው። በተለይ በክልሉ ቤንች ሸኮ ዞን ሰላምና ልማትን በማስተሳሰር እየተሠራ ያለው ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ዶክተር ፍጹም አሰፋ አስገንዝበዋል። የሱፐርቪዥኑ ዓላማ በእቅድ የወረዱ ተግባራት አፈጻጸምን በማየት ጉድለቶችን ለመሙላት የሚያስችል ድጋፍ ማድረግ እንደሆነ ገልጸው "ህዝቡ ተጠቃሚ የሚሆንበት ልማት እንዲሳካ በትብብር እንሠራለን" ብለዋል። በዞኑ ደቡብ ቤንች ወረዳ የተመለከቱት ከ2 ሺህ 500 ሄክታር በላይ የክላስተር ሙዝ ልማት ለሌሎች አካባቢዎች ትልቅ ተሞክሮ የሚሆን መልካም ተግባር መሆኑን አንስተዋል። በዞኑ የፀጥታ ችግርን ከማኅበረሰቡ ጋር በቅንጅት ለመፍታት በተሰራ ስራ አሁን ላይ የልማት መነቃቃት እንዲኖር ማድረጉን አድንቀዋል። በዞኑ ሌማት ትሩፋት ላይ እየታዩ ያሉ ጅምር ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸው ገልጸው በማር ምርት ላይ ያለው የተሻለ አፈጻጸም በእንቁላል ዶሮና በሥጋ ምርት እንዲስፋፉ አቅጣጫ ማስቀመጣቸውን ተናግረዋል። ባጠቃላይ በተግባር አፈጻጸም የታዩ መልካም ተሞክሮዎች እንዲስፋፉና ክፍተት ያለባቸውን አይቶ የገጠማቸው ችግር የሚፈታበትን መንገድ የማመላከት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። የግብርና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ፍቅሩ ረጋሳ በበኩላቸው የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት እንደ ሀገር ትኩረት የተደረገባቸው የልማት ሥራዎች አተገባበርን መሬት ወርዶ በማየት መደገፍ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። ለአብነትም በሌማት ትሩፋትና የግብርና ምርቶችን በስፋት በማምረት የምርት መጠን አሳድጎ የተሻሻለ ኑሮን ማየት ዓላማ ተደርጎ እየተሠራ ያለው ተግባር ተስፋ ሰጪ ነው ብለዋል። በዞኑ በቡናና ቅመማ ቅመም ምርት ያለውን እምቅ አቅም ወደ ዓለም ገበያ በብዛት በማቀላቀል ሀገራዊ ኢኮኖሚ ላይ አስተዋጽኦ እንዲኖረው የመደገፍ ሥራ ይጠበቅብናል ሲሉም አክለዋል ። የቤንች ሸኮ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካብቲን በበኩላቸው የፌዴራል አመራሮች ለሥራ ክትትልና ድጋፍ እስከታችኛው መዋቅር ድረስ መውረዳቸው ለዞንና ወረዳ አመራሮች የሥራ መነቃቃትና ሞራልን የሚሰጥ ነው ብለዋል። የህዝቡን ኑሮ ለማሻሻል የሱፐርቪዥን ቡድኑ የሰጣቸው የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ጉድለቶችን በመሙላት ለተሻለ አፈጻጸም እንደሚሠሩ ተናግረዋል። የቤንች ሸኮ ዞን ለቡናና ፍራፍሬ ምርት ተስማሚ በመሆኑ በንቅናቄ የማልማት ሥራ ላይ ትኩረት ማድረጋቸውን የዞኑ ግብርና፣ ደንና አካባቢ ጥበቃና ኅብረት ሥራ መምሪያ ኃላፊ አቶ መስፍን ጉብላ ተናግረዋል። በዞኑ ከ240 ሺ ሄክታር በላይ የቡናና ቅመማ ቅመም ማሳ መኖሩን ጠቅሰዋል።
የኅብረት ሥራ ማኅበራት የአሠራር ሥርዓታቸውን በማሻሻል ዘመናዊ አገልግሎት ለመስጠት የተጀመረው ሪፎርም ሊጠናከር ይገባል
Mar 18, 2024 59
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ የኅብረት ሥራ ማኅበራት የአሠራር ሥርዓታቸውን በማሻሻል የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት የጀመረው የሪፎርም ሥራ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ ገለፁ። የአዲስ አበባ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን "የማኅበራትን ኃብትና ንብረት ከብክነት በመጠበቅ የአባላቱንና የኅብረተሰብ ተጠቃሚነትን እናረጋግጥ" በሚል መሪ ኃሳብ ሲያካሂድ የቆየው ንቅናቄ ማጠቃለያ መርኃ ግብር እየተካሄደ ነው። የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ በመዲናዋ የኅብረት ሥራ ማኅበራት እየተስተዋሉ ያሉ ክፍተቶችን ለመሙላት የሪፎርም ተግባራት እየተከናወኑ ነው። ሪፎርሙ የማኅበራቱን የአሠራር ሥርዓት የሚያዘምን እንዲሁም ጠንካራ አደረጃጀት በመፍጠር የቁጥጥርና የክትትል ሥራ ለመሥራት እንደሚያስችል ጠቁመዋል። ይህም ብቻ ሳይሆን በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ኃይል ለማፍራትና የአሠራር ሥርዓቱን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እንደሚያግዝም ነው ያብራሩት። ከተማ አስተዳደሩ የኅብረት ሥራ ማኅበራት አሠራራቸውን በማሻሻል ምርቶችን በስፋት ወደ ገበያ እንዲያቀርቡ ለማስቻል ድጋፍ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። በመሆኑም ኮሚሽኑ የጀመረው የሪፎርም ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ነው ያስገነዘቡት። በመድረኩ የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የሁሉም ክፍለ ከተማና ወረዳ የኅብረት ሥራ ማኅበራት ተወካዮች ተገኝተዋል።
በአቶ አዲሱ አረጋ የተመራ የፌዴራል የሱፐርቪዥን ቡድን በኮንሶ ዞን በካራት ወረዳ እየተሰሩ ያሉ የልማት ስራዎችን ጎበኘ
Mar 18, 2024 56
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦በአቶ አዲሱ አረጋ የተመራ የፌዴራል ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች የተካተቱበት የሱፐርቪዥን ቡድን በኮንሶ ዞን ካራት ወረዳ እየተሰሩ ያሉ የልማት ስራዎችን ጎብኝቷል። ቡድኑ ምርትና ምርታማነትን ከማሳደግ አኳያ በካራት ዙሪያ ወረዳ ፉጩጫ ቀበሌ የሌማት ትሩፋት፣ የደረሰ የቀይ ሽንኩርት ምርት፣ የነጭ ሽንኩርት ምርትና የሙዝ እርሻ ስራዎችን የመስክ ምልከታ አድርጎል፡ በቀበሌው በመስኖ እየለማ የሚገኝ የበጋ ስንዴ ልማት አበረታች ጅምር መሆኑንም ቡድኑ በምልከታው አስታውቋል። ቡድኑ እየተሰራ ያለው ስራ ጥሩ መሆኑን ገልጾ በተለይም ከበጋ መስኖ ጋር በተያያዘ ይበልጥ መስራት እንደሚጠበቅ አሳስቧል። በተጨማሪም የህብረተሰብ የልማት ተሳትፎ፤ትምህርት ለትውልድ፤ድርቅን ለመቋቋም የተደረጉ ጥረቶች፤የወጣቶች የስራ እድል ፈጠራ ልዩ ምልከታ በቡድኑ ተደርጎባቸዋል፡፡ የሱፐርቪዥን ቡድኑ ቀጥሎ በወረዳው አርካሌ ደራ ቀበሌ በ49 ሚሊዮን ብር ካፒታል እየተገነባ የሚገኘውን እና የአንድ ቀን ጫጬት ማስፈልፈያ፣ የስጋ ዶሮ እርባታ፣ የእንቁላል ማምረቻ እና ለእንስሳት መኖ ማቀነባበሪያ የሚያገለግል ፕሮጀክት ግንባታም ጎብኝቷል። በምልከታው የታዩ ጠንካራ ተግባራትን በማስቀጠልና በማስፋት የህብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ እንደሚገባ አመልክቷል፡፡ ውስንነት የተስተዋለባቸው አፈፃፀሞችን በተደራጀ መልኩ ማጠናከር እንደሚገባም ቡድኑ ማመልከቱን ከብልጽግና ፓርቲ ማህበራዊ ትስስር ገጽ ለማወቅ ተችሏል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሥራ ቆይታቸውን ያጠናቀቁትን የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ኡስማን ዲዮን አመሰገኑ
Mar 18, 2024 216
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሥራ ቆይታቸውን ያጠናቀቁትን የዓለም ባንክ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ኡስማን ዲዮን አመስግነዋል። የዓለም ባንክ ላለፉት አመታት ለኢትዮጵያ ላደረገው ያላሰለሰ ድጋፍ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማመስገናቸውን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ያሰፈሩት መረጃ ያመላክታል።
በሰላም ሚኒስትር ብናልፍ አንዷለም የተመራ የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን በጨንቻ ዙሪያ ወረዳ የሚገኝ የአፕል ችግኝ ብዜት ማዕከልን ጎበኘ
Mar 18, 2024 51
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በሰላም ሚኒስትሩ አቶ ብናልፍ አንዷለም የተመራ የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን በጨንቻ ዙሪያ ወረዳ የሚገኝ የአፕል ችግኝ ብዜት ማዕከል እና የምርት ማሳን ጎብኝቷል። የሰላም ሚኒስትሩ በችግኝ ብዜትም ሆነ በአፕል ምርታማነት ዙሪያ ውጤታማ ተግባር መመልከታቸውን ገልፀዋል። የአፕል ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ለመገንባትም ከባለሀብቶች እና ከረጂ ድርጅቶች ጋር በመተባበር ማቀድ እንደሚገባ አመላክተዋል። ግብርና እና ኢንዱስትሪ ተያይዘው የሚያድጉ ዘርፎች መሆናቸውን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፤ ከጥሬ ዕቃ አቅርቦት ባሻገር ለአግሮ ፕሮሰሲንግ ትኩረት ሊሰጥ እንደሚገባ መግለጻቸውን ከብልጽግና ፓርቲ የተገኘው መረጃ ያመላክታል። በወረዳው በግብርና ምርት ትልቅ አቅም እንዳለ መመልከታቸውን የቡድኑ አባላት ገልጸው፤ ከአፕል ጋር ተያይዞ ዝርያዎችን በዞኒንግ ስፔሻላይዝድ የማድረግ ስራ ሊሰራ እንደሚገባም ጠቁመዋል። በወረዳው 1 ሺህ 315 ሄክታር መሬት በአፕል መሸፈኑም በመረጃው ተመላክቷል።
አለም አቀፍ የሸማቾች ቀን በአዲስ አበባ ተከበረ
Mar 18, 2024 57
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ 11ኛው አለም አቀፍ የሸማቾች ቀን 'በህብር መብታችንን እናስከብር' በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ ተከበረ። በዓሉ በአለም ለ41ኛ ጊዜ በኢትዮጵያ ደግሞ ለ11ኛ ጊዜ 'በህብር መብታችንን እናስከብር' በሚል መሪ ሃሳብ በንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር አዘጋጅነት ተከብሯል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ እንዳለው መኮንን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በዓሉ የሚከበረው ሽማቾች ስለሚገዙት ምርት ጥራት፣ ባህሪና ዋጋ የማወቅ መብት እንዳላቸው ለማስገንዘብ ነው። ለሸማች መብት መከበር ከመንግስት ባሻገር የብዙ ባለድርሻ አካላት ርብርብ እንደሚጠይቅ ጠቁመዋል። የዛሬው መድረክ የሸማቹን መብት ለማስከበር ከራሱ ከሸማቹና ከመንግስት ባሻገር የሁሉንም ርብርብ የሚጠይቅ መሆኑን ለማስገንዘብና ከተሳታፊዎች ጋር የጋራ መግባባት ለመፍጠር ጭምር እንደሆነ ተናግረዋል። ሸማቹ መሠረታዊ ምርቶችንና አገልግሎቶችን የማግኘት፣ ከአደጋ የመጠበቅ፣ መረጃ የማግኘት ፣ አማራጭ የማግኘትና ለሎችም መብቶች እንዳሉት መረጃዎች ያመለክታሉ። በበዓሉ አከባበር ላይ ባለድርሻ አካላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች በክልሉ የልማት ስራዎችን እየተመለከቱ ነው
Mar 18, 2024 39
ሆሳዕና፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዶክተር ዓለሙ ስሜ የተመራው የፌዴራል ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል እየተከናወኑ የሚገኙ የተለያዩ የልማት ስራዎችን እየጎበኙ ነው። የሥራ ሃላፊዎቹ በመንግሥት፣ በግል ባለሀብትና በህብረተሰብ ተሳትፎ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ተግባራትን እየጎበኙ ነው። የሥራ ሃላፊዎቹ ዛሬ ከጠዋቱ ጀምረው በክልሉ በሃላባ ዞን ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር የተለያዩ የልማት ስራዎች ምልከታ እያደረጉ የሚገኙ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ የአስና ዱቄት ፋብሪካ ይገኝበታል። የአስና ዱቄት ፋብሪካ ባለቤት አቶ የአብነህ ማቲዎስ ለሥራ ሃላፊዎቹ በሰጡት ማብራሪያ ፋብሪካው በ2004ዓ.ም በ78 ሚሊዮን ብር ካፒታል ተገንብቶ ስራ ጀምሯል። በቀን ከ1 ሺህ 120 ኩንታል በላይ ዱቄት የሚያመርት ሲሆን ከ40 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል መፈጠሩንም ገልጸዋል። ከትንሽ ሥራ ተነስተው አሁን ላሉበት ደረጃ መድረሳቸውንና ለሌሎች መትረፋቸውን ነው አቶ የአብነህ የተናገሩት። ሥራን ሳይንቁ መስራታቸውና ትጋት እንዲሁም በሁሉም ነገር ያለውን የሥራ አማራጭ የመጠቀም ተስፈኝነት ለዚህ እንዳበቃቸው አክለዋል። "እንደ ሀገር በርካታ የልማት አማራጮች አሉን" ያሉት አቶ የአብነህ፤ ጠንክሮ መስራትና በአካባቢው ያለውን አማራጭ ማየት እንዲሁም ሰላም እንዲሰፍን የሚጠበቅብንን መወጣት ከሁላችን ይጠበቃል ሲሉም ተናግረዋል። በቀጣይም አመራሮቹ በክልሉ ስልጤና ምስራቅ ጉራጌ ዞኖችን ጨምሮ ሌሎች አካባቢዎች በመዘዋወር ድጋፍን መሠረት ያደረገ የመስክ ምልክታቸውን እንደሚያከናውኑ ተገልጿል።