ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
በማዕከሉ የሚሰለጥኑ ሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማላቅ አስፈላጊውን ድጋፍ ይደረጋል - ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Mar 27, 2025 33
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፡- በማዕከሉ የሚሰለጥኑ ሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማላቅ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ ያደርጋል ሲሉ የስራ እና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ። ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ከ"ለነገዋ" የሴቶች ተሃድሶና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከል የሥራ ኃላፊዎች ጋር ተወያይተዋል፡፡ በማዕከሉ የሚሰለጥኑ ሴቶችን ተጠቃሚነት ማላቅ ላይ ባተኮረው የውይይት መድረክ የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሂርጳሳ ጫላ እና ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ኤልሻዳይ ክፍሌ ተገኝተዋል፡፡ ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በውይይቱ እንደገለጹት፤ በማዕከሉ የሚሰለጥኑ ሴቶች በሥራ ገበያው ላይ ተፈላጊ የሆነ ክህሎት ባለቤት እንዲሆኑ በማድረግ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማላቅ ይሰራል፡፡ በክህሎት ልማትና ሥራ ዕድል ፈጠራ መስኩ ያሉ ዕድሎችን እንዲጠቀሙ ከማድረግ ባሻገር የማዕከሉ አቅም ቀጣይነት ባለው መልኩ እንዲያድግ ሚኒስቴሩ አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ ያደርጋል ማለታቸውን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡
በዞኑ የበጋ መስኖ ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳደገ መጥቷል
Mar 27, 2025 40
አምቦ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ምእራብ ሸዋ ዞን የበጋ መስኖ ልማት የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደገ ምምጣቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የአዝእርት ልማትና የእጽዋት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ደጀኔ ገመቹ ለኢዜአ እንደተናገሩት፥ አርሶ አደሩ የዝናብ ወቅትን ጠብቆ ከማምረት ወጥቶ በበጋ መስኖ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት መስራቱን ተናግረዋል። አርሶ አደሩ በተለይም በበጋ መስኖ አትክልትን በማልማት ኢኮሚያዊ ተጠቃሚነቱን ከማሳደግ ባለፈ የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝ መድረጉን ጠቅሰዋል። በዞኑ የከርሰ ምድርና የገፀ ምድር ውኃ ሀብትን በመጠቀም ዘንድሮ በበጋ መስኖ በመጀመሪያው ዙር 30ሺህ 164 ሄክታር መሬት ላይ አትክልትና ፍራፍሬ በማልማት 3ሚሊዮን ኩንታል ምርት መሰብሰቡን ተናግረዋል፡፡ ባህላዊና ዘመናዊ የመስኖ አውታሮችን በመጠቀም ጎመን፣ ሽንኩርት፣ ሰላጣ፣ ቲማቲም፣ ካሮት፣ ድንችና ስኳር ድንች መልማታቸውን አንስተዋል። በሁለተኛ ዙርም 9ሺህ 224 ሄክታር መሬት በማልማት 4 ሚሊዮን ኩንታል የአትክልት ምርት ለመሰብሰብ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡ በበጋ መስኖ ልማቱ ከተሰማሩት አርሶ አደሮች መካከል የቶኬ ኩታዬ ወረዳ ነዋሪ አቶ አለሙ ፈይሳ፤ የውሀ አማራጮችን በመጠቀም በመስኖ ያለሙትን ቀይ ሽንኩርትና ቲማቲም ለገበያ በማቅረብ ከ250ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ የአምቦ ወረዳ አርሶ አደር በቀለ መገርሳ በበኩላቸው በመጀሪያው ዙር በመስኖ ካለሙት የጓሮ አትክልት ሽያጭ 300ሺህ ብር ገቢ ማግኘታቸውን አስታውሰዋል። በሁለተኛ ዙርም የተለያዩ የጓሮ አትክልቶችን ማልማት መጀመራቸውን አክለዋል።
በከተማ ልማታዊ ሴፍትኔት ፕሮግራም በመሳተፍ ሰርተን በቆጠብነው ገንዘብ የተሻለ ገቢ እያመነጨን እንገኛለን - የአክሱም ከተማ ተጠቃሚዎች
Mar 27, 2025 38
አክሱም፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፡- በከተማ ልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም በመሳተፍ የሥራና የቁጠባ ባህላቸውን በማሳደግ የተሻለ ገቢ እያመነጩ መሆናቸውን በአክሱም ከተማ በፕሮግራሙ የታቀፉ ነዋሪዎች ገለጹ። በከተማው ለፕሮግራሙ ማስፈፀሚያ 112 ሚሊዮን ብር የተመደበ ሲሆን ከ6ሺህ በላይ ነዋሪዎችም ከሚከፈላቸው የወር ደመወዝ ላይ በመቆጠብ እና ተጨማሪ ብድር በመውሰድ በጀመሩት ስራ የተሻለ ህይወት እንዲመሩ እንዳደረጋቸውም ተናግረዋል። ወይዘሮ አባዲት አስመላሽ በከተማው በልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም በሥራ ላይ እንደሚገኙ ተናግረው በየወሩ ከሚከፈላቸው 3ሺህ ብር የተወሰነውን በመቆጠብና በወሰዱት ተጨማሪ ብድር 50 ጫጩቶችን ገዝተው ወደ ዶሮ እርባታ ስራ መግባታቸውን ገልፀዋል። በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥም የ300 ዶሮዎችና የአንዲት የወተት ላም ባለቤት መሆን መቻላቸውን ገልጸው፣ ዛሬ ላይ የተበደሩትን ገንዘብ ሙሉ በሙሉ መልሰው አምስት ልጆቻቸውን ሳይቸገሩ እያስተማሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ሌላኛዋ የአክሱም ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ማሚት ወልደ ገብርኤል በፕሮግራሙ በመሳተፋቸው ሥራን፣ የቁጠባ ባህልንና ከአነስተኛ ገንዘብ በመነሳት ኑሮን ማሸነፍ እንደሚቻል ልምድ ማግኘታቸውን ገልፀዋል። በ20ሺህ ብር የጀመሩት የዶሮ እርባታ ቁጥር አንድ መቶ በማድረስ የእርባታ ስራውን እያቀላጠፉ መሆኑን ተናግረዋል። በየወሩ ከሚሰጠው ሶስት ሺህ ብር 20 በመቶውን በመቆጠብ ከጓደኞቹ ጋር በመተባበር ከተማውን አቋርጦ ከሚወርደው ወንዝ ውሃ በመጥለፍ የመስኖ ልማት መጀመራቸውን የገለጸው ደግሞ ወጣት አስማረ ትኩእ ነው። 28 አባላትን አደራጅቶ ወደ መስኖ ልማት የገባው የእነ አስማረ ማህበር የጓሮ አትክልት እያመረቱ ለገበያ ማቅረብ መጀመራቸውን ተናግሯል። የማህበሩ አባል ወይዘሮ ለታይ ገብረመድህን በበኩላቸው፣ የመስኖ ልማት ስራ ከጀመሩ ወዲህ አራት ልጆቻቸውን ከማስተማር ባለፈ የመኖርያ ቤት መገልገያ ቁሳቁሶችን ማሟላት መቻላቸውን አመልክተዋል። የአክሱም ከተማ ልማታዊ ሴፍትኔት ፕሮግራም አስተባባሪ ወይዘሮ ለተሚካኤል ኪዳነማርያም፣ በከተማው በመጀመሪያው ዙር 6ሺህ 293 ሰዎች ተመልምለው ወደ ሥራ መሰማራታቸውና ለፕሮግራሙ ማስፈጸሚያ 112 ሚሊዮን ብር መመደቡን ገልጸዋል። ነዋሪዎቹ በየወሩ ከሚከፈላቸው ገንዘብ ቀንሰው በመቆጠብ በተለያዩ የሥራ ዘርፎች እየተሳተፉ ናቸው ያሉት አስተባባሪዋ፣ የዕለት ኑራቸውን ከማሸነፍ አልፈው አነስተኛ ሃብት ማፍራት ጀምረዋል ብለዋል።
በቦረና ዞን የተገነቡ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቁ
Mar 27, 2025 41
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2017 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን የተገነቡ በፀሐይ ሃይል የሚሰሩ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል። በማስጀመሪያ ስነ ስርዓቱ ላይ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ጨምሮ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። በአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ የከርሰ ምድር ውሃ ፕሮጀክት አካል ከሆኑት ፕሮጀክቶች መካከል 100 ኩዩቢክ ሜትር ሪዘርቬየር ያለው የሮምሶ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት ከ106 ሚሊዮን 300 ሺህ ብር በላይ በሚሆን ወጭ ተገንብቶ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል። ፕሮጀክቱ ከአራት ሺህ በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን የመጠጥ ውሃ ተጠቃሚ እንደሚያደርግ እና 27 ሺህ በላይ የሚሆኑ እንስሳቶችን ውሃ እንዲያገኙ የሚያስችል መሆኑን የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። የቦረና ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ በሪሶ ጋኖ በዞኑ በስድስት ወረዳዎች ተግባራዊ እየተደረገ ያለው ፕሮጀክት ድርቅ ቢከሰት ህብረተሰቡ እንዳይፈናቀልና የተረጋጋ የመማር ማስተማር ሂደት እንዲኖር አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። ሚኒስቴሩ ለፕሮጀክት ግንባታው ላደረገው ድጋፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። በተያያዘ ዜና በቦረና ዞን ከ131 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እየተገነባ ያለው የዲዳ ያቤሎ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት እና በዞኑ ከ83 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ውጪ የተገነባው የኤርደር የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት በቅርቡ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምሩ ተገልጿል። ሁሉም የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች በሶላር ኢነርጂ እንደሚሰሩ ሚኒስቴሩ አስታውቋል።
በዞኑ የአርሶ አደሩን የማምረት አቅም ለማሳደግ የሚያስችል የተፈጥሮ ማዳበሪያ በስፋት እየተዘጋጀ ነው
Mar 27, 2025 42
ጭሮ ፤መጋቢት 18/2017 (ኢዜአ)፡-በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የአርሶ አደሩን የማምረት አቅም ለማሳደግ የሚያስችል የተፈጥሮ ማዳበሪያ በስፋት በማዘጋጀት ለመስኖ ልማትና ለበልግ አዝመራ ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑን የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በጽህፈት ቤቱ የግብርና ቴክኖሎጂ ማስፋፋትና አፈር ለምነት ስራ ሂደት አስተባባሪ አቶ ታሪኩ አሰፋ ዛሬ ለኢዜአ እንደገለጹት ባለፉት ዓመታት መንግስት ለግብርናው ዘርፍ በሰጠው ከፍተኛ ትኩረት የአርሶ አደሩ የማምረት አቅም እየጨመረ መጥቷል። በተለይ እየጨመረ የመጣውን የአርሶ አደሩን የማዳበሪያ ፍላጎት ለማሟላት በአካባቢው የሚገኙ ጸጋዎችን ተጠቅሞ የተፈጥሮ ማዳበሪያ እንዲያመርት ሰፊ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመዋል። በመሆኑም በዚህ ዓመት ብቻ በዞኑ 15 ወረዳዎች የሚገኙ ከ400 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ያሳተፈ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ዝግጅት በስፋት ሲከናወን መቆየቱን ተናግረዋል። በተያዘው ዓመት የተዘጋጀውን ከ14 ሚሊዮን ሜትር ኩዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ 300 ሺህ ሄክታር መሬት የማልማት አቅም ያለው ሲሆን አርሶ አደሩ ለመስኖ ልማትና ለበልግ አዝመራ ጥቅም ላይ እያዋለው መሆኑን አስረድተዋል። እንደ አስተባባሪው ገለፃ በዚህ ዓመት የተዘጋጀው ኮምፖስት ከአምናው ጋር ሲነፃፀር ከ7 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ ብልጫ አለው። በዞኑ ጭሮ ወረዳ ጃርሶ ቀበሌ አርሶ አደር ሙሜ ጠሀ በሰጡት አስተያየት የፋብሪካ ማዳበሪያ ከጊዜ ወደ ጊዜ ዋጋው እየጨመረ በመምጣቱ የተፈጥሮ ማዳበሪያን በስፋት ማዘጋጀት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። በመሆኑም በዚህ አመት ከ100 ኩንታል በላይ የተፈጥሮ ማዳበርያ በማዘጋጀት ለበልግ አዝመራ ጥቅም ላይ ለማዋል እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። ይህም ለኬሚካል ማዳበሪያ የሚያወጡትን ወጪ ከመቀነስ ባለፈ ምርታማ እንደሚያደርጋቸውም ተናግረዋል። በወረዳው የጃርሶ ቀበሌ አርሶ አደር አህመድ አሊዪ በበኩላቸው በባለሙያዎች ምክር በመታገዝ በአጭር ጊዜ የሚደርስ ኮምፖስት በማዘጋጀት ጥቅም ላይ እያዋሉ መሆኑን ገልፀዋል። ዘንድሮ ባዘጋጁት የተፈጥሮ ማዳበርያም በጉድጓድ ውሃና አነስተኛ መስኖ የጓሮ አትክልት በማልማት ከምርት ሽያጭ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስረድተዋል። የተፈጥሮ ማዳበሪያ የአፈር ለምነትን የሚጨምር መሆኑን በተግባር አረጋግጠናል የሚሉት አርሶ አደሮቹ በቀጣይም ስራውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን በበጀት ዓመቱ ስምንት ወራት ከ44 ሺህ በላይ ለሆኑ ወጣቶች የስራ እድል ተመቻቸ
Mar 27, 2025 34
ነገሌ ቦረና ፤ መጋቢት 18/2017 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ቦረና ዞን በበጀት ዓመቱ ስምንት ወራትከ44 ሺህ በላይ ለሆኑ ወጣቶች የስራ እድል መመቻቸቱን የዞኑ የስራ እድል ፈጠራና ክህሎት ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የእቅድ ክትትልና ግምገማ ባለሙያ አቶ ሊበን ሀለኬ በዞኑ በበጀት ዓመቱ 66 ሺህ 500 ወጣቶችን ወደ ስራ ለማስገባት ታቅዶ ሲሰራ ቆይቷል። በበጀት ዓመቱ ባለፉት ስምንት ወራት 44 ሺህ 561 ወጣቶች ወደ ስራ የገቡ ሲሆን፤ ከዚህም መካከል ሴቶችና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተመራቂዎች እንደሚገኙበት ገልጸዋል፡፡ አቶ ሊበን ሀለኬ እንዳሉት የስራ እድል ፈጠራውም በማዕድን ማውጣትና ግብይት፣ በግብርና፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በግንባታና በሸቀጣ ሸቀጥ አገልግሎት መሆናቸውን ተናግረዋል። በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች 693 ሄክታር የማምረቻ ቦታ፤ 13 የመሸጫ ሼዶችና ሁለት የእርሻ መኪናዎች ድጋፍ መደረጉንም ሃላፊው ጠቅሰዋል፡፡ ለስራ ዘርፎቹ አንቀሳቃሾች ከሲንቄ ባንክና ከተለያዩ የፋይናንስ ተቋማት 78 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር ብድር መሰጠቱንም አስታውቀዋል፡፡ በዚህም ወጣቶቹ በተሰማሩበት የስራ ዘርፍ ለተጠቃሚዎች ምርትና አገልግሎታቸውን እያቀረቡ ነው ብለዋል። እንዲሁም በዞኑ በዚህ ዓመት ወደ ስራ ለሚገቡ ወጣቶች የብድር አገልግሎት እና የማምረቻና የመሸጫ ቦታ መመቻቸቱን አስታውቀዋል፡፡ ከስራ እድሉ ተጠቃሚ ወጣቶች መካከል የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪ ናትናኤል ለማ ከአራት ባልደረቦቹ ጋር በሸቀጣ ሸቀጥ ንግድ መሰማራቱን ተናግሯል፡፡ ወጣቱ ባለፉት ስምንት ወራት የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦችን በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑን ገልጾ፤ በዚህም በገቢው እራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ከመርዳት አልፎ እየቆጠቡ መሆኑንም ተናግሯል። ወጣት ናትናኤል እንዳለው የመሸጫ ሱቅ ድጋፍና የብድር አገልግሎትም ተመቻችቶላቸዋል፡፡ የዚሁ ከተማ ነዋሪ ወጣት ሙክታር ኡመር በበኩሉ መንግስት ያመቻቸላቸው የመስሪያ ቦታና የብድር አገልግሎት በራስ አቅም ሰርቶ መለወጥ የሚያስችል ነው ብሏል፡፡ ለወጣቱና አራቱ ባልደረቦቹ ከነገሌ ከተማ አስተዳደር የ360 ሺህ ብር ብድርና የመሸጫ ሱቅ ድጋፍ መመቻቸቱንም ገልጿል፡፡ "ድጋፉ ወጣቶች ባለን እውቀትና ክህሎት ሰርተን እንድንለወጥ፤ ምርትና አገልግሎትን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ለሌሎችም እንድንተርፍ ያስችለናል" ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዓለም አቀፍ የቅድመ ክፍያ ማስተር ካርድ ይፋ አደረገ
Mar 27, 2025 56
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዓለም አቀፍ የፕላስቲክ እና ቨርቹዋል የቅድመ ክፍያ ማስተር ካርድን ይፋ አድርጓል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከዓለም አቀፉ የክፍያ ተቋም ማስተር ካርድ ጋር በመተባበር የማስተር ካርድ ቅድመ ክፍያ ሥርዓትን አስጀምሯል። በይፋ ማድርጊያ ስነ-ስርአቱ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቤ ሳኖ፣ የማስተር ካርድ የአፍሪካ ፕሬዚዳንት ማርክ ኤሊዮትን ጨምሮ የንግድ ባንክ እና የማስተር ካርድ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቤ ሳኖ በወቅቱ እንደገለጹት ባንኩ የዲጂታል ቴክኖሎጂን በማሳደግ አገልግሎቱን እያዘመነ ይገኛል። የቅድመ ክፍያ ማስተር ካርዱ የባንኩን ዲጂታል አገልግሎት ይበልጥ እንደሚያዘምነው አስታውቀዋል። የማስተር ካርድ አፍሪካ ፕሬዚዳንት ማርክ ኤሊዮት በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያስጀመረው ዲጂታል አገልግሎት አለም አቀፍ አገልግሎቱን ይበልጥ የሚያቀላጥፍ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይ ማስተር ካርድ ከባንኩ ጋር ዲጂታል ቴክኖሎጂን የማሳደግ ስራ ላይ በጋራ እንደሚሰራም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት መብቷን ለማሳካት እያደረገች ያለውን ጥረት ማጠናከር ይገባናል - ምሁራን
Mar 27, 2025 39
ድሬዳዋ/ሆሳዕና፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ):- ኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት መብቷን የዲፕሎማሲ አማራጭን በመጠቀም ለማሳካት እያደረገች ያለውን ጥረት ማጠናከር ይገባናል ሲሉ ምሁራን ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በባህር በር ዙሪያ ሰሞኑን ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለቀረበላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ መስጠታቸው ይታወሳል። በዚህ ላይ በመመሰረት የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት በድሬዳዋ እና በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲዎች የሚሰሩ ምሁራንን አነጋግሯል። በድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የአለም አቀፍ ህግ መምህር አለምሰገድ ደጀኔ እንዳሉት፤ በታላቁ የህዳሴ ግድብ ላይ የተሰራው የተቀናጀ ውጤታማ የዲፕሎማሲ ስራ የባህር በር ጥያቄን ለማሳካት ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል። ለሶስት አስርት ዓመታት የተዳፈነው የሀገራችን የባህር በር የማግኘት አለም አቀፍ መብት በይፋ የአደባባይ አጀንዳ መደረጉ ወሳኝ እርምጃ መሆኑንም ገልጸዋል። ሀገራችን በተባበሩት መንግስታት ህግ መሰረት በዲፕሎማሲያዊ መንገድ የባህር በር የማግኘት መብቷ የተረጋገጠ መሆኑንም አንስተዋል። የተጀመረውን ጥረት በተጠናና በተቀናጀ ዲፕሎማሲያዊ መንገዶች የአለም አጀንዳ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን ምሁሩ ጠቁመው፤ ለዚህም የሀገራችን የአለም የዲፕሎማቲክ ማዕከል መሆኗ፣ ከፍተኛ የህዝብ ቁጥር ባለቤትነትና ለአለም ሰላም መከበር እያበረከተች ያለችው ታላቅ ስራ ጥሩ መደላድሎች ይሆናሉ ብለዋል። የኢትዮጵያን የባህር በር የማግኘት መብት ለማሳካት የአሁኑ ትውልድ እና ምሁራን ዋና አጀንዳ ማድረጉን አጠናክረን መቀጠል አለብን ሲሉም አብራርተዋል። በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የታሪክ መምህርና ተመራማሪ አስራት ኤርሞሎ(ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ በሴራ የባህር በር ባለቤትነቷን እንድታጣ መደረጉን አስታውሰው፤ መንግስት የትውልዱ ጥያቄ የሆነውን ይህን ጉዳይ በዲፕሎማሲ አማራጭ ለማሳካት የጀመረውን ጥረት ማጠናከር አለበት ብለዋል፡፡ የሀገር ደህንነት ስጋትን ከመታደግ ባለፈ ከውጪ ለሚገቡ ምርቶች የሚወጣን ከፍተኛ የውጪ ምንዛሪ በማስቀረት የሀገሪቱን ዕድገት ለማፋጠንና ተወዳዳሪ ኢኮኖሚን ለመገንባት የባህር በር ባለቤትነት አይተኬ ሚና እንዳለው ነው የተናገሩት፡፡ መንግስት የባህር በር የማግኘት ጥረትን በሰላማዊ መንገድ ተፈፃሚ እንዲሆን እያደረገ ስላለው ጥረት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት መግለፃቸው ተገቢ ያልሆኑ አስተያየቶችና ውዥንብሮችን ያረመና ያጠራ መሆኑንም አውስተዋል፡፡ ሰላማዊና ዲፕሎማሲ አማራጮችን በመጠቀም ሀገሪቱ የባህር በር ማግኘት የምትችልባቸው ሰፊ አማራጮች እንዳሏት ጠቁመው የተጀመረውን ጥረት ማጠናከር ይገባናል ብለዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ወደ ስልጣን ከመጡ ወዲህ የብሔራዊ ጥቅምን ለማስከበር እየተነሱ ካሉ ጉዳዮች መካከል አንዱ የባህር በር የማግኘት ጉዳይ እንደሆነ የተናገሩት በዩኒቨርሲቲው የፖለቲካል ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር ሙሉዓለም ኃይለማርያም ናቸው። እንደ ኢትዮጵያ ላሉ በማደግ ላይ ለሚገኙ ሀገራት የውጪ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ፣ የገቢና ወጪ ንግድን ለማሳለጥ የባህር በር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ገልጸዋል፡፡ ለአብነትም የዲፕሎማሲ ስኬት ማሳያ የሆነው የአንካራው ስምምነትን ጨምሮ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ጉዳይ ዓለም አቀፍ አጀንዳ እንዲሆንና የበርካታ ዓለም ሀገራትን ድጋፍ እያገኘ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡
በማእከላዊ ጎንደር ዞን ገበያን የማረጋጋት ተግባር እየተከናወነ ነው
Mar 27, 2025 46
ጎንደር፤ መጋቢት 18/2017 (ኢዜአ)፡- በማእከላዊ ጎንደር ዞን የምርት አቅርቦትን በማሻሻል ገበያን የማረጋጋት ተግባር እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ አስታወቀ፡፡ የመምሪያው ሃላፊ አቶ አይቸው ታረቀኝ ለኢዜአ እንደገለጹት በዞኑ ገበያን ለማረጋጋት እንዲቻል ለምርት አቅርቦት ስራ የሚውል ከ70 ሚሊዮን ብር በላይ ተመድቦ ወደ ስራ ተገብቷል፡፡ በምርት አቅርቦትና ስርጭት ሂደትም ዩኒየኖች፣ የሸማቾች ማህበራትና ኢንተርፕራይዞች እየተሳተፉ መሆናቸውን ተናግረዋል ። በሸማቾች ማህበራትና በነጋዴዎች በኩል ባለፉት ሁለት ወራት ከ33ሺ ኩንታል በላይ የግብርና ምርቶች ማቅረብ መቻሉን ጠቅሰዋል ። ከቀረቡት የግብርና ምርቶች መካከልም ጤፍ፣ በቆሎና ማሽላ እንደሚገኙበት ጠቁመው ከገበያ ዋጋ በኩንታል ከ200 እስከ 400 ብር ቅናሽ እንዳላቸውም አመልክተዋል። መጪውን የረመዳንና የትንሳኤ ጾም ፍቺ ምክንያት በማድረግም ለህብረተሰቡ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን ለማቅረብ የሚያስችሉ ዝግጅቶች መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ በአላቱን ምክንያት በማድረግ ከ270ሺ ሊትር በላይ የምግብ ዘይት ጨምሮ አንድ ሺ 325 ኩንታል ስኳር፣ 368 ኩንታል የዳቦ ዱቄትና 7ሺ ኩንታል ሽንኩርት ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ የሚያስችል ስራ መጀመሩን አመልክተዋል፡፡ በዞኑ ዘጠኝ የወረዳ ዋና ከተሞችም ሸማቹንና አምራቹን በቀጥታ ለማገናኘት የሚያስችሉ የንግድ ትርኢትና ባዛሮችን ለማዘጋጀት ታቅዶ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑንም ጠቅሰዋል ። በከተሞች የሚታየውን የዋጋ ንረትና የምርት አቅርቦት እጥረት ለመፍታት የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች ለነዋሪዎች እየቀረቡ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጸሃይ ሁለገብ የገበሬዎች ህብረት ስራ የኒየን ስራ አስኪያጅ አቶ ይሁኔ ዳኘው ናቸው፡፡ ዩኒየኑ ጤፍን ጨምሮ 71ሺ ኩንታል የተለያዩ የምግብ ሰብሎችን ከአርሶአደሩ በመግዛት በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ መጀመሩን ተናግረዋል ። እስካሁንም ከ7ሺ ኩንታል በላይ ጤፍ በኩንታል ከገበያ ዋጋ እስከ 400 ብር ቅናሽ በማድረግ መቅረቡን ተናግረዋል ። ዩኒየኑ ባቋቋመው የምግብ ዘይት ፋብሪካ ያመረተውንና ከአዲስ አበባ ከሚገኙ አምራች ድርጅቶች ያስመጣውን ከ370ሺ ሊትር በላይ የምግብ ዘይት በተመጣጣኝ ዋጋ ለህብረተሰቡ በማቅረብ ገበያውን በማረጋጋት የድርሻውን ማበርከቱን ተናግረዋል፡፡ የጎንደር ከተማ ነዋሪ የሆኑት አቶ ታምሩ በላይና አቶ እሸቴ መንግስቴ በዩኒየኑ በኩል ጤፍና የምግብ ዘይት በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘታቸውን ጠቁመው የቀረበው ምርት ገበያውን በማረጋጋት በኩል ድርሻው የላቀ መሆኑን አመልክተዋል ።
መንግስት ጠንካራና እና በአግባቡ የተደራጀ የፋይናንስ ስርአት በመዘርጋት የመንግስት ሃብት ለሃገራዊ ልማት እንዲውል እያደረገ ነው
Mar 27, 2025 63
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፦ መንግስት ጠንካራና እና በአግባቡ የተደራጀ የፋይናንስ ስርአት በመዘርጋት ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ምንጮች የሚሰበሰብ ሃብት ለሃገራዊ ልማት እንዲውል እያደረገ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስቴር አስታወቀ። ኤፍ ኤስ ዲ ኢትዮጵያ ከገንዘብ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ነጠላ ሂሳብ አስተዳደር "ለመንግስት ገንዘብ አስተዳደር አስፈላጊ መሳሪያ" በሚል መሪ ሃሳብ አውደ ጥናት እያካሄደ ነው። በመድረኩ የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ኢዮብ ተካልኝን ጨምሮ የኤፍኤስዲ የቦርድና የማኔጅመንት አባላት ተገኝተዋል። የገንዘብ ሚኒስቴር ዴኤታ ኢዮብ ተካልኝ በዚሁ ወቅት መንግስት የገንዘብ እንቅስቃሴውን ለማዘመን በጀመረው ጥረት ሂደቱን በዲጂታል ስርአት ለመለወጥ አበረታች ስራ እያከናወነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የመንግስትን ሃብት ወጪ ቆጣቢ ፣ ቀልጣፋና ውጤታማ በሆነ ስርአት ማስተዳደር ሀገራዊ ግዴታችን ነው ብለዋል። መንግስት ጠንካራና እና በአግባቡ የተደራጀ የፋይናንስ ስርአት በመዘርጋት ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ፣ ከእርዳታ ፣ ከብድር እና ከሌሎች ምንጮች የሚሰበሰብ ሃብት በአግባቡ ለሃገራዊ ልማት እንዲውል እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ይህ እውን እንዲሆን ደግሞ የትሬዥሪ ነጠላ አካውንት ስርአት ቁልፍ ሚና አለው ብለዋል። የትሬዠሪ ነጠላ አካውንት ስርአት በበርካታ የባንክ ሂሳቦች ተበታትነው የሚገኙ የመንግስት ገንዘቦችን ወደ አንድ ቋት የሚያመጣ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህም በተበታተነ የሂሳብ አያያዝ የሚከሰቱ ችግሮችን በማቃለል ዘመናዊ የመንግስት ጥሬ ገንዘብ አያያዝ አስተዳደር እንዲኖር አስቻይ ሁኔታ ይፈጥራል ብለዋል። ዘመናዊ የመንግስት ጥሬ ገንዘብ አያያዝ ደግሞ ቀልጣፋ፣ ውጤታማ፣ ግልፅ እንዲሁም ተጠያቂነት የሰፈነበት የመንግስት የፋይናንስ አስተዳደር እንዲኖር ያስችላል ነው ያሉት። ይህም መንግስት ለአጭር ጊዜ ብድሮች የሚያወጣቸውን ወጪዎች በመቀነስ ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት ጠቅሰዋል። እንዲሁም የተናበበ የገንዘብና ፊሲካል ፖሊሲ እንዲኖር ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳለው ነው የጠቀሱት። ለነጠላ ገንዘብ አስተዳደር ትግበራ ዘላቂነትና ውጤታማነት በተለይም የመንግስት መስሪያ ቤቶች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።
በፈጠራ በሰራው ማሽን የወዳደቁ የውሃ ፕላስቲኮችንና ጠርሙሶችን ፈጭቶ ዳግም አምርቶ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እያቀረበ ያለው ወጣት
Mar 27, 2025 37
የ32 ዓመቱ ወጣት ዳዊት ተክለኃይማኖት ተወልዶ ያደገው ሽሬ እንዳስላሴ ከተማ ነው። የአንደኛ ደረጃ ትምህርቱንም በዚያው ተከታትሎ 10ኛ ክፍል ሲደረስ በሽሬ ፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ በአውቶሞቲቭ በደረጃ አራት ተመርቋል። በተመረቀበት ሙያም የመኪና ጥገና ስራ ተቀጥሮ ለአራት ዓመታት ሰርቷል። ዳዊት ከልጅነቱ እስከ እድገቱ ጎበዝ፣ ስራ ወዳድ፣ አዳዲስ ፈጠራዎችን የሚሞክር ታታሪ መሆኑን የሚያውቁት ሁሉ ይናገራሉ። በዚሁ መንገድም እየሰራ እራሱንና ቤተሰቡን እያገዘ በታታሪነቱ ቀጥሏል። በአንድ አጋጣሚ በሚኖርበት አካባቢ ጥቅም ላይ ውለው በተጣሉ የፕላስቲክ ጠርሙሶች የተደፈነ የውሃ ማፋሰሻ ቦይ ሲከፈት ይመለከታል፤ ወዲያውኑም ከወዳደቁ የፕላስቲክ ውጤቶች ምን መስራት ይቻላል የሚለውን ጥያቄ በውስጡ አሰላሰለ። የፕላስቲክ ውጤቶች ወደ ጥቅም እንደሚቀየሩ በአንድ ወቅት ከቅርብ ጓደኛው መስማቱ ትዝ አለው። በጊዜው ስለ ጉዳዩ ሰምቶ በውስጡ ደጋግሞ ከማሰብ ውጪ አማራጭ አልነበረውም። የጎርፍ መውረጃ ቦይን በመዝጋት ችግር እየፈጠረ ያለን የፕላስቲክ ቁስ ወደ ጥቅም የመቀየር ሃሳብን ሲያወጣና ሲያወርድ ከረመ። የሚኖርባት ሽሬ ከተማ ሞቃታማ በመሆኗ ነዋሪው በተለምዶ የታሸገ ውሃ ተጠቅሞ የሚጥለው ፕላስቲክ በብዛት ስላለ የጥሬ ዕቃ ችግር እንደማይገጥመው አረጋግጧል። በመሆኑም ሙሉ ትኩረቱን የትም ተጥለው የሚገኙትን የፕላስቲክ ውጤቶች የሚፈጭ ማሽን ማፈላለግ ላይ አደረገ። ማሽኑንም ለማግኘት ወደ አዲስ አበባ አቀና። ዳዊት በወቅቱ የፈለገው ሁለት ዓይነት ማሽኖችን ነበር፤ አንደኛው የፕላስቲክ ውጤቶቹን የሚፈጭ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ አጥቦ ለዳግም ጥቅም የሚያዘጋጅ። ሆኖም የማሽኑ ዋጋ ውድና ካለው ካፒታል አንጻር የማይሞከር ሆኖ አገኘው፤ በመሆኑም ወደ ሽሬ ከተማ በመመለስ ማሽኑን ራሱ ከወዳደቁ ብረቶች በመስራት ከሁለት ዓመት በፊት ስራ አስጀመረ። ማሽኑን ሰርቶ ለማጠናቀቅ ሃያ ሁለት ቀናት ብቻ እንዳስፈለጉት የገለፀው ወጣት ዳዊት በተበደረው አንድ ሚሊዮን ብር ስራ መጀመሩን ይናገራል። ከወዳደቁ ብረቶች በሰራው ማሽን የወዳደቁ የውሃ ፕላስቲኮችንና ጠርሙሶችን ፈጭቶና አምርቶ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ እያቀረበ ያለው ወጣት በስራው ስኬታማና ትርፋማ ሆኖ ሌሎችንም ቀጥሮ በማሰራት ላይ ይገኛል። በዚሁ ስራው ቤተሰቦቹን በማስተዳደር ላይ ይገኛል። ከስራ ጅማሬው በአንድ ዓመት ውስጥ ከአንድ ሺህ ኩንታል በላይ የተፈጨ የፕላስቲክ ውጤቶችን ለሀገር ውስጥና ለቱርክ ገበያ በማቅረብ ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን ገልጿል። በአንድ ሚሊዮን ካፒታል የተጀመረው ስራ በአሁኑ ወቅት ወደ 20 ሚሊዮን ብር ከፍ ማለቱን የገለፀው ዳዊት አሁን ላይ ለ67 ወገኖች የስራ ዕድል በመፍጠር ለወርሃዊ የደመወዝ ክፍያም ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደሚያደርግ ተናግሯል። የስራ ዕድሉ ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል ወጣት ሰላም ማሞ፤ በተፈጠረላት የስራ ዕድል ተጠቃሚ በመሆን ከራሷ አልፋ ቤተሰብ እያስተዳደረች መሆኑን ተናግራለች። የዳዊት ስራ ወዳድነትና ባለመታከት ለውጤት የመብቃት ጥረት ለብዙ ወጣቶች ምሳሌ እንደሚሆንም ተናግራለች። ቆሻሻ ጥቅም እንዳለው የተማርኩበት ስራ ነው በማለት አስተያየታቸውን የሰጡት አቶ እስጢፋኖስ ገብረመድህን በወር 11 ሺህ 500 ብር እየተከፈላቸው ቤተሰባቸውን እያስተዳደሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በየወሩ በማገኘው ደመወዝ ቤተሰቤን ለማስተዳደር ችያለሁ ያለችው ደግሞ አበባ በረኸ ነች። የዳዊት የጥረት ውጤት ከራሱ አልፎ ለብዙዎቻችን ስራ ያስገኘና ለቤተሰባችንም መተዳደሪያ በመሆኑ ልናመሰግነው እንወዳለን ብለዋል። የከተማዋ የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት አስተባባሪ አቶ አብራሃለይ ፍቃዱ በበኩላቸው የወጣቱን የስራ እንቅስቃሴ ለማበረታታት ስራውን አስፍቶ እንዲሰራ የሚያደርገው የመሬት አቅርቦት እንደሚመቻችለትም ተናግረዋል።
የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶቹ ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮቻችን መፍትሄ የሚሰጡ ናቸው - የምስራቃዊ ሲዳማ ዞን ነዋሪዎች
Mar 27, 2025 33
ሀዋሳ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል የምስራቃዊ ሲዳማ ዞን የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያሳድጉ የምስራቃዊ ሲዳማ ዞን ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ የክልሉ መንግስት የህብረተሰቡን መልካም አስተዳደር ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የጀመራቸው የመንገድ፣ የድልድይና የውሃ ፕሮጀክቶች ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮቻቸው መፍትሄ የሚሰጡ መሆናቸውን ነዋሪዎቹ ተናግረዋል፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል የቡራ ወረዳ ነዋሪ አቶ በቀለ ዱሹሼ ቀደም ሲል በአካባቢው የሚስተዋለው የንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ችግር እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ የክልሉ መንግስት ይህንን ችግር ለመቅረፍ የገነባው የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት የአካባቢውን ህዝብ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦች ችግር የቀረፈ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የጨቤ ጋምቤልቱ ወረዳ ነዋሪው አቶ ገናሌ ፍጡንጌ በበኩላቸው ቀበሌያቸውን ከወረዳ ጋር የሚያገናኘው ድልድይ በመገንባቱ ቀደም ሲል የነበረውን የትራንስፖርት እጥረት መፍታቱን ተናግረዋል፡፡ በሌላ በኩል ምርታቸውን ለገበያ ለማቅረብና የግብርና ግብዓቶችን ለማጓጓዝ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም ገልጸዋል፡፡ በወረዳው እየተሰራ ያለው የመንገድና የድልድይ ግንባታ ዘርፈ ብዙ ችግራቸውን እንደሚቀርፍ የተናገሩት ደግሞ የአሮሬሳ ወረዳ ነዋሪው አቶ ንጉሴ ቦጋለ ናቸው፡፡ የሲዳማ ክልል መንገድ ልማትና ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ታምሩ ታፌ በበኩላቸው እስከ በጀት ዓመቱ ማጠናቀቂያ ከ1ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ የገጠር መንገዶች ግንባታና ጥገና ለማጠናቀቅ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ ውስጥ 261 ኪሎ ሜትሩ የገጠር መንገድ ግንባታ ሲሆን ቀሪው ጥገና መሆኑን ጠቅሰው ለፕሮጀክቶቹ ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ከመንገድ ፕሮጀክቶቹ በተጨማሪ ዘንድሮ በልዩ ትኩረት ከተጀመሩ 12 የድልድይ ግንባታ ፕሮጀክቶች አራቱ የተጠናቀቁ ሲሆን ቀሪዎቹ እስከ በጀት ዓመቱ ማብቂያ ይጠናቀቃሉ ብለዋል፡፡
ለጅቡቲ መጠጥ ውኃ ፕሮጀክት የኤሌክትሪክ መሰረተ-ልማት ዝርጋታ ተከናወነ
Mar 27, 2025 58
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፦ ለጅቡቲ ድንበር ተሻጋሪ የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክት የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማት ዝርጋታ መከናወኑን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስታወቀ። የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክቱ ዝርጋታ በሁለት ምዕራፍ ተከፍሎ ሲከናወን መቆየቱንም አስታውቋል። በመጀመሪያው ምዕራፍ 8 ሜጋዋት ኃይል፣ 36 ኪሎ ሜትር የመስመር ዝርጋታ እንዲሁም 8 ባለ 1250 ኬቪኤ ትራንስፎርመር ተከላ ተከናውኗል ብሏል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር እንዲሁም ኦንያድ የተሰኘው የጅቡቲ ውኃ ፕሮጀክት ባቀረቡት ተጨማሪ ኃይል ጥያቄ መሠረት ሁለተኛው ምዕራፍ ስራ መጠናቀቁን የአገልግሎቱ መረጃ ያመለክታል። ለውኃ ፕሮጀክቱ 12 ነጥብ 2 ሜጋ ዋት ተጨማሪ ኃይል መጠየቁንና ከአዲጋላ ሰብስቴሽን ከሚወጣው መስመር 8 ሜጋ ዋት በ1250 ኬቪኤ 8 ትራንስፎርመሮች፤ ቀሪው 4 ነጥብ 2 ሜጋ ዋት ደግሞ በ28 ባለ 500 ኪቪኤ፣ 315 ኬቪኤ እና 400 ኪቪኤ ትራንስፎርመሮች ኃይል እንዲያገኝ ተደርጓል ሲልም ገልጿል። ፕሮጀክቱ ካለው ሀገራዊ ፋይዳ አንፃር የአካባቢውን በርሃማ የአየር ፀባይ በመቋቋም ስራውን በስኬታማነት ማጠናቀቅ መቻሉንም አገልግሎቱ አስታውቋል። በአሁኑ ወቅት የፕሮጀክቱ የሁለተኛው ምዕራፍ ሥራ ተጠናቆ ርክክብ እየተደረገ እንደሚገኝም በመረጃው ተመልክቷል።
የሀረር ከተማ የመጀመሪያው ዙር ኮሪደር ልማት የኤሌክትሪክ መስመር ማዛወር ስራ ተጠናቋል- አገልግሎቱ
Mar 27, 2025 50
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፡- በሀረር ከተማ እየተከናወነ ባለው የመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማት የመካከለኛና ዝቅተኛ የኤሌክትሪክ ማሰራጫ መስመር ማዛወር እና ማሻሻያ ስራ በተለዩ 18 ሳይቶች ላይ ሙሉ በሙሉ መጠናቀቁን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት አስታወቀ፡፡ በዚህም በአጠቃላይ 1ሺህ 107 የእንጨት እና የኮንክሪት ምሰሶዎች፣ 40 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የኤሌክትሪክ መስመር እንዲሁም 12 የተለያየ መጠን ያላቸው ትራንስፎርመሮች የማዛወር ስራ ተከናውኗል ብሏል፡፡ በመጀመሪያው ዙር የመስመር ማዛወር ስራ የተከናወነው በሀረር ከተማ ከአራተኛ እስከ ስታዲየም፣ ከአጅፕ እስከ ሰላም አደባባይ፣ ከሀረር ቢራ እስከ ገስታውስ፣ ከአራተኛ እስከ ቀይ መስቀል እንዲሁም ከኢማም አህመድ ስታዲየም እስከ ገስታውስ የሚሸፍን መሆኑንም ጠቁሟል። ቀደም ሲል የነበረው የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት በዋናነት ያረጀ በመሆኑ አካባቢዎቹ ላይ የኃይል መቆራረጥ ይከሰት የነበረ ሲሆን፤ አሁን ላይ በተሰራው የማዛወር ስራ የኃይል መቆራረጥን በዘላቂነት ሊቀርፍ በሚችል መልኩ ደረጃውን የጠበቀ የመስመር ዝርጋታ ተከናውኗል ነው ያለው አገልግሎቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፡፡ በተጨማሪም በሁለተኛው ዙር በሚከናወነው የኮሪደር ልማት 1 ነጥብ 66 የመካከለኛ እና 2 ነጥብ 45 ኪሎ ሜትር የዝቅተኛ መስመር የማዛወር ስራ የሚከናወን ሲሆን፤ በአጠቃላይ 523 የሚሆኑ የኤሌክትሪክ መስመር ተሸካሚ ምሰሶዎች እና 4 የተለያየ መጠን ያላቸው ትራንስፎርመሮችን ለማዛወር የቅድመ ዝግጅት ስራ ተጠናቋል ሲልም አስታውቋል። የሁለተኛው ዙር የመስመር ማዛወር ስራ የሚከናወነው በከተማዋ ከስላሴ ቤተክሰርስቲያን እስከ የሺመቤት ትምህርት ቤት፣ ከደሴ ሆቴል እስከ ሙጢ አደባባይ፣ አባድር ፕላዛ አካባቢ እስከ ቡዳ በር አካባቢዎች የሚከናወን ነው ብሏል በመግለጫው፡፡ በአጠቃላይ በኮሪደር ልማቱ እየተከናወነ የሚገኘው የኃይል መስመር ማዛወር ስራ በከተማዋ ለኮሪደር ልማት በተለዩ ዋና ዋና መስመሮች ላይ የሚኖረውን የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ከማዘመን ባሻገር የኃይል መቆራረጡን በዘላቂነት ለመቀነስ መልካም አጋጣሚ የፈጠረ መሆኑንም አመላክቷል፡፡
ሚኒስቴሩ በነዳጅ አጠቃቀም የቴክኖሎጂ ሥርዓት ለሌሎች ተቋማት አርዓያ መሆን አለበት - ቋሚ ኮሚቴው
Mar 26, 2025 79
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስቴር በነዳጅ አጠቃቀም የቴክኖሎጂ ሥርዓት ለሌሎች ተቋማት አርዓያ መሆን እንዳለበት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። በሒሳብ ኦዲት ግኝት ላይ ሚኒስቴሩ የወሰዳቸው የማስተካከያ እርምጃዎች የሚያበረታቱ መሆናቸውን ቋሚ ኮሚቴው ገልጿል። ቋሚ ኮሚቴው የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስቴርን የ2015 ዓ.ም በጀት ዓመት የኦዲት ግኝት ሪፖርት የእርምት እርምጃን ገምግሟል። ቋሚ ኮሚቴው በንብረት አስተዳደር፣ በሒሳብ ብልጫና ማነስ የተመዘገቡ የኦዲት ግኝት ጉድለቶችን አስመልክቶ ጥያቄዎችን በጽሁፍ አቅርቧል። በዚሁ ወቅት የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሰረት ዳምጤ እንደገለጹት፤ ሚኒስቴሩ የንብረት አስተዳደር፣ ሒሳብ ብልጫና ማነስ የኦዲት ጉድለቶችን ለማስተካከል የወሰደው የእርምት እርምጃ በበጎ የሚታይ ነው። ገቢና ወጪን፣ ቋሚና አላቂ ዕቃዎችን በቴክኖሎጂ ሥርዓት ለማስተዳደር የተጀመረው ስራ አበረታች ቢሆንም ቀጣይነት ያለው ስራ የሚጠይቅ መሆኑንም አስገንዝበዋል። በትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር የነዳጅ አጠቃቀም ሥርዓት ለሌሎች መስሪያ ቤቶች አርዓያ መሆን የሚያስችለውን ስራ መስራት እንዳለበት አመልክተዋል። የፌዴራል ዋና ኦዲተር ምክትል ዋና ኦዲተር አቶ አበራ ታደሰ፤ ሚኒስቴሩ በማነስና መብለጥ የተመዘገቡ የቅድመ ክፍያ፣ የማያዣ፣ የእሴት ታክስና ጥሬ ገንዘብ ግኝቶችን ማስተካከሉን አረጋግጠዋል። የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ(ዶ/ር) በንብረት አስተዳደር፣ በማነስና መብለጥ የተመዘገቡ የሒሳብ ጉድለቶች ላይ ቀጣይነት ያለው የእርምት እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ገልጸዋል። የተቋሙ ተሽከርካሪዎች የነዳጅ አጠቃቀምን ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሮኒክስ የመረጃና ግብይት ሥርዓት ለማስገባት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ዴንጌ ቦሩ በበኩላቸው፤ የንብረት አስተዳደር፣ የወጪና ገቢ ሒሳብ አያያዞችን በተቀናጀ የዲጂታል ሥርዓት ማድረግ የሚያስችል መሰረተ ልማት እየተፈጠረ መሆኑን ነው ያመለከቱት። በምክር ቤቱ የመንግስት ወጪ አስተዳደር እና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሺመቤት ደምሴ(ዶ/ር)፤ የሒሳብና ንብረት አስተዳደር ጉድለቶችን ለማሻሻል በተደረገው ጥረት ልክ በነዳጅ አጠቃቀም ሥርዓት ላይ ለተቋማት አርዓያ መሆን አለበት ብለዋል። ሚኒስቴሩ ለተቋማት ምሳሌ የሚሆን ከሰው እጅ ንክኪ የገንዘብ ገቢና ወጪ የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ሥርዓት መዘርጋት እንዳለበትም አሳስበዋል።
ሚኒስቴሩ በክዋኔ የኦዲት ግኝት መሰረት እያከናወነ ያለው ተግባር ሊሻሻል እንደሚገባ ተመላከተ
Mar 26, 2025 53
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በክዋኔ የኦዲት ግኝት መሰረት ክፍተቶቹን ለማስተካከል እያከናወነ ያለው ተግባር ሊሻሻል እንደሚገባ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። ቋሚ ኮሚቴው የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የ2015/16 በጀት ዓመት የክዋኔ ኦዲት ሪፖርት ላይ ተወያይቷል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የሺእመቤት ደምሴ (ዶ/ር) እንዳሉት ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከፕሮጀክቶች አፈፃፀም ጋር ተያይዞ ዝቅተኛ አፈፃፀም ማሳየቱን ጠቁመዋል። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በመንግስትም ይሁን በአጋር ድርጅቶች ድጋፍ ለሚሰራቸው ለእያንዳንዱ ፕሮጀክቶች የዳሰሳና የአዋጭነት ጥናት አለመስራቱ በፕሮጀክቶች አፈፃፀም ለታዩ ክፍተቶች መፈጠር ምክንያት መሆኑን አብራርተዋል። በቀጣይም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የዳሰሳና የአዋጭነት ጥናት በመስራት ክፍተቶቹን ማረም እንደሚገባ እና ክትትልና ድጋፍ ማድረግ እንደሚያስፈልግም አሳስበዋል፡፡ አያይዘውም የፕሮጀክቶች መዘግየትና መጓተት ብሎም ቅድሚያ መሰጠት ያለባቸው ፕሮጀክቶችን ቅድሚያ የመስጠት ችግር መኖሩን ጠቁመው፣ በተያዘላቸው ጊዜ ያላለቁ ፕሮጀክቶች ወቅታዊ ሁኔታ የማይታወቅ ሲሆን፣ የፋይናንስና የፊዚካል አፈፃፀማቸው የተስማሚነት ችግር እንዳለበትም ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም ፕሮጀክቶች ሳይጠናቀቁ አቋርጦ በጀቱን ወደ ሌላ ፕሮጀክት በማዘዋወር ሂደት ረገድ የህግ፣ የመመሪያ፣ የአሰራር ጥሰት የታየበት በመሆኑ ሊታረም ይገባል ነው ያሉት። ከሰው ሀብት ጋር ተያይዞም መስሪያ ቤቱ ሰራተኞችን በሪኮመንዴሽን የሚቀጥርበት ሁኔታ ህግና ስርዓት ያልተከተለ በመሆኑ ሰራተኞችን አወዳድሮ ሊቀጥርና አሰራሩ ሊታረም እንደሚገባም አሳስበዋል። ከንብረት ማስመለስ ጋር በተያያዘም ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የለቀቁና ጡረታ የወጡ ሰራተኞች ያልመለሷቸውን በጥቅል ከፍተኛ ዋጋ ያላቸውን የመንግስትና የህዝብ ሀብት በአግባቡ የማስመለስ ስራ መስራት አለበት ብለዋል። የፌደራል ዋና ኦዲተር ወይዘሮ መሰረት ዳምጤ በበኩላቸው በኦዲት ሪፖርቱ ላይ የቀረበው አፈጻጸም በተወሰኑ ፕሮጀክቶች ላይ ያተኮረ መሆኑን ጠቁመው፣ ተቋሙ አሁን የሚሰራቸው በርካታ ስራዎች መኖራቸውንና ከዚህ ተነስቶም አጠቃላይ ስራውን ሊፈትሽና ሊያሻሽል እንደሚገባ አሳስበዋል። ተጠያቂ የሆኑ አካላትንም በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ተጠያቂ አድርጎ ሪፖርት ማድርግ ይገባልም ብለዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በበኩላቸው ተቋሙ ለሀገር በርካታ ስራዎች እየሰራ መሆኑን አስታውሰው፣ ከፕሮጀክቶች፣ ከንብረት ማስመለስ፣ ካለአግባብ ከተከፈሉ ክፍያዎች፣ ከሰራተኞች ቅጥር ጋር ተያይዞ በአፈፃፀም ሂደት ጉድለቶች መኖራቸውንና የእርምት እርምጃዎች እንደሚወሰዱ ጠቁመዋል፡፡ አያይዘውም ወጪ ወጥቶ ያልተሰሩ ስራዎች ካሉ ፍተሻ እንደሚደረግም ነው ሚኒስትሩ የተናገሩት፡፡ የፕሮጀክት ውል ሲያዝ ጠቅላይ አቃቤ ህግ ማወቅና ማማከር ያለበት በመሆኑ በቀጣይ በአግባቡ የሚፈፀም መሆኑን ጠቁመው፣ በአጋር አካላት በተለይ በአለም ባንክ አማካኝነት የሚሰሩ ፕሮጀክቶች ያሉንን ሀገራዊ ስትራቴጂዎችና ንድፎች መሰረት ተደርጎ እንደሚቀረፁ አስረድተዋል። አገር አቀፍ አንድምታ ያላቸውን ጉዳዮች ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር ተነጋግረን ነው የምንፈርመው ያለ እርሱ ይሁንታ አንሰራም ያሉ ሲሆን በተመሳሳይም የፍትህ ሚኒስቴር ይሁንታ የሚያስፈልጋቸው ከሆነም ለሚኒስቴሩ እናሳውቃለን ማለታቸውን ከምክር ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
ኢትዮጵያ እና ኬንያ አንድ አለቅ የድንበር ጣቢያዎች ማስፋፋት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ተወያዩ
Mar 26, 2025 72
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን እና የኬንያ ገቢዎች ባለስልጣን የአንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት ጣቢያዎችን/One Stop Border Posts/ ማስፋፋት እና በሌሎች የጉምሩክ ጉዳዮች ላይ በጋራ መስራት የሚያስችል ውይይት ተደርጓል፡፡ በውይይቱ የሁለቱ ሀገራት ሌሎች ባለድርሻ ተቋማትም መሳተፋቸውን የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን መረጃ ያመላክታል፡፡ በውይይቱ የጉምሩክ ኮሚሽን ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ፣ በኢትዮጵያ የኬንያ አምባሳደር ጆርጅ አሪና፣ የዓለም ባንክ የምስራቅ አፍሪካ ተወካዮች፣ የኢትዮጵያ ጉምሩክ ኮሚሽን ከፍተኛ አመራሮች እና ሌሎች ባለድርሻ መስሪያ ቤቶች ተወካዮች ተሳትፈዋል፡፡ የጉምሩክ አስተዳደሮች ንግድን የማሳለጥ እና የድንበር ቁጥጥር ስርዓትን የማጠናከር ቁልፍ ሚና እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡ የጉምሩክ ተቋማት ይህን ሚናቸውን ለመወጣት ከአቻ ተቋማት ጋር በቅንጅት መስራት እንዳለባቸው አስገንዝበው ኮሚሽኑ ከኬንያ ገቢዎች ባለስልጣን ጋር በትብብር እየሰራ ያለውን ስራ ይበልጥ መጠናከር እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡ ከዓመታት በፊት አገልግሎት መስጠት የጀመረው በኢትዮጵያና በኬንያ ድንበር የሚገኘው የሞያሌ አንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት ማዕከል ተደጋጋሚ ፍተሻዎችን በማስቀረት የተፋጠነ የጉምሩክ አገልግሎት እንዲኖር ማስቻሉን አስረድተዋል፡፡ የአፍሪካ ኢኮኖሚያዊ ውህደት በአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጠና እና በሌሎች አካባቢያዊ የኢኮኖሚ ብሎኮች አማካኝነት እየተፋጠነ መሆኑን ገልጸው ኮሚሽኑ ኢትዮጵያ በዚህ ሂደት ውስጥ ግንባር ቀደም ሚናዋን እንድትወጣ የበኩሉን ጥረት እያደረገ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡ በኢትዮጵያ የኬንያ አምባሳደር ጆርጅ አሪና በበኩላቸው፤ በኬንያና በኢትዮጵያ ድንበር ላይ የአንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት ማዕከል መገንባት የሁለቱን ሀገራት እድገት ለማፋጠን ዓይነተኛ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል፡፡ ውይይቱ ተጨማሪ የጋራ አንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት መስጫ ጣቢያዎችን ሱፍቱ እና ራሙ በሚባሉ የድንበር አካባቢዎች መገንባት ስለሚቻልበት ሁኔታ ብሎም በሁለቱ ሀገራት መካከል የንግድ እና የህዝብ- ለህዝብ ትስስርን ለማጠናከር ዓለማ ያደረገ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡ በተጨማሪም ሁለቱ ተቋማት ትብብራቸውን ማጠናከር የሚያስችል የትብብር ስምምነት ለመፈራረም የሰነድ ዝግጅት በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ ከስምምነት ላይ ደርሰዋል፡፡ የአንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት(One stop border post) በአጎራባች ሀገሮች ድንበር ላይ በጋራ የሚገነቡና የድንበር ቁጥጥር የሚያደርጉ አገልግሎት ሰጭ ተቋማት በአንድ ቦታ እንዲገኙ በማድረግ ተደጋጋሚ ፍተሻዎችን በማስቀረት የሸቀጦችንና የሰዎችን እንቅስቃሴን ለማፋጠን የሚረዱ ማዕከላት ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ እና በኬንያ ድንበር የተገነባው የሞያሌ አንድ አለቅ የድንበር አገልግሎት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እና በቀድሞው የኬንያ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ህዳር 30 ቀን 2013 ዓ.ም ተመርቆ ስራ መጀመሩ የሚታወስ ነው፡፡
የሶስት ከተሞች የመካከለኛ መስመር ግንባታ ስምምነት ተፈረመ
Mar 26, 2025 70
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዊልኪንስ ኢንጅነሪንግ ኩባንያ ከተሰኘ ድርጅት ጋር የሶስት ከተሞች የመካከለኛ መስመር ግንባታ ስምምነት ተፈርሟል። ስምምነቱ አገልግሎቱ በቀጣይ ለመገንባት በዕቅድ ከያዛቸው የ10 ከተሞች የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ማሻሻያና አቅም ማሳደግ ፕሮጀክት አካል የሆኑት የደበረብርሃን፣ ሱሉልታ እና ቢሾፍቱ ከተሞች የመካከለኛ መስመር የመልሶ ግንባታና ማሻሻያ ፕሮጀክትን የተመለከተ ነው፡፡ የፕሮጀክት ግንባታ ስምምነቱ የተከናወነው በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎትና በጋናው ዊልኪንስ ኢንጅነሪንግ ኩባንያ መካከል ነው፡፡ በስምምነቱ ላይ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ስራ አስፈፃሚ ጌቱ ገረመው(ኢ/ር) እንዳሉት ፕሮጀክቱ በከተሞቹ ያለውን የኤሌክትሪክ አቅርቦት አስተማማኝ በማድረግ ደንበኞች አስተማማኝ የኤሌክትሪክ አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ በተያዘለት የጊዜ ገደብና የጥራት ደረጃ መጠናቀቅ እንዳለበት ማሳሰባቸውን ከአገልግሎቱ የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡ የዊልኪንስ ኢንጅነሪንግ ኩባንያ ተወካይ ኦማን ፍሪምፖንግ በበኩላቸው ፕሮጀክቱን በተያዘው ጊዜና የጥራት ደረጃ አጠናቀሙ እንደሚያስረክቡ ገልፀዋል፡፡ የመልሶ ግንባታ ስራው 386 ኪሎ ሜትር የመካከለኛ መስመር የሚሸፍን የመልሶ ግንባታ እና 315 ኪሎ ቮልት አምፒር አቅም ያላቸው 87 አዲስ ትራንስፎርመሮች እንደሚተከሉም ተገልጿል፡፡ ፕሮጀክቱ ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ የኤሌክትሪክ የመቆራረጥ ድግግሞሹን 45 በመቶ እና የቆይታ ጊዜውንም በ50 በመቶ እንደሚቀንስ ተጠቁሟል፡፡ በተጨማሪም የእንጨት ምሶሶዎችን ወደ ኮንክሪት መቀየር፣ ያልተሸፈኑ የኤሌክትሪክ መስመርን በተሸፈኑ ገመዶች የመቀየር ስራ እንደሚሰራ ተመላክቷል፡፡ ፕሮጀክቱ የሚከናወነው ከአለም ባንክ በተገኘ 17 ነጥብ 3 ሚሊየን ዶላር ብድር ሲሆን ግንባታውም በሁለት አመት ውስጥ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ግብርናውን በመካናይዜሽን በመደገፍ ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
Mar 26, 2025 64
ባህርዳር፣ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- በግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ እየተመዘገበ ያለውን እድገት ለማስቀጠል በመካናይዜሽን የተደገፈ እንዲሆን ትኩረት መደረጉን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር) ገለጹ። አዲሱን የግብርናና ገጠር ልማት ፖሊሲ የሚያስተዋወቅ መድረክ በባህር ዳር ከተማ ዛሬ ተካሂዷል። ሚኒስትር ዴኤታው መለስ መኮንን (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ እንደገለጹት ፈጣንና ቀጣይነት ያለው የግብርና ምርታማነት እንዲኖር የግብርናና ገጠር ልማት ፖሊሲው መሻሻሉን ገልጸዋል። ፖሊሲው በአለም ላይ ያለውን የተሻለውን የአመራረት ዘይቤ ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ የዘርፉን መልካም አጋጣሚዎችና የመልማት አቅምን አሟጦ ለመጠቀም የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የተሻሻለው የግብርና ፖሊሲም ቀጣይነት ያለው የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ፣ የምግብ ሉአላዊነትን ማረጋገጥ፣ ሀገራዊ ምግብና ስነ-ምግብ ዋስትናን ማጎልበት ላይ ያተኮረ መሆኑን አስረድተዋል። ለዚህም የግብርና መካናይዜሽንና አዳዲስ ቴክኖሎጅዎችን በመጠቀም ለኢንዱስትሪው ዘርፍ ግብአትና ለወጭ ንግድ በቂ ምርት ወጥ በሆነ መልኩ ማምረት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በሰብል፣ በእንስሳት፣ በደንና ሌሎች የግብርና ዘርፎች ተወዳዳሪነት በማረጋገጥ በአገር ደረጃ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር ለማምጣት በሚሰራው ስራ አጋዥ ሚና የሚጫወት ነው ብለዋል። ለፖሊሲው ተፈጻሚነት በየደረጃው ያለው አመራር፣ ባለሙያውና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በቁርጠኝነት መረባረብ እንደሚገባቸው አሳስበዋል። የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳደር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) በበኩላቸው የግብርናውን ዘርፍ በቴክኖሎጅ የተደገፈ አሰራር መተግበር ይገባል ብለዋል። በዚህም ለገበያና ለኢንዱስትሪ ግብአት የሚሆን ምርት ላይ በማተኮር ለመረባረብ የፖሊሲው መሻሻል አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመው የክልሉ መንግስት ለተግባራዊነቱ ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የክልሉ የገጠር ዘርፍ አሰተባባሪና የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) እንደገለጹት በክልል ደረጃ ዛሬ የተጀመረው ፖሊሲውን የማስተዋወቅ ስራ እሰከ ታች ድረስ ተጠናክሮ ይቀጥላል። ፖሊሲውን መሰረት በማድረግም ለባለሙያዎች፣ አርሶ አደሮችና ሌሎች አጋር አካላት የግንዛቤ ፈጠራ ስራ በቀጣይነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በመድረኩ የፌደራልና የክልል ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችና የዘርፉ አመራሮች ተገኝተዋል።
የሸገር ከተማ በበጀት ዓመቱ ቀሪ ወራት ከሁለት ሺህ በላይ ባለሀብቶችን ለመቀበል ተዘጋጅቷል
Mar 26, 2025 53
ሸገር፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፦ የሸገር ከተማ አስተዳደር በተያዘው በጀት ዓመት ቀሪ ጊዜ ውስጥ ከሁለት ሺህ በላይ ባለሀብቶችን ለመቀበል መዘጋጀቱን የከተማው ምክትል ከንቲባ አቶ ጉዮ ገልገሎ ገለፁ። ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ተቋማት የተውጣጡ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን አመራርና ባለሙያዎች በሸገር ከተማ የተለያዩ የልማት ኢንቨስትመንት እንቅስቃሴዎችን ጎብኝተዋል። ምክትል ከንቲባው በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት ሸገር ከኢንቨስትመንት አንጻር ምቹ ሁኔታዎችን ያሟላ ከተማ ነው። አስተዳደሩ ይህን መልካም እድል በመጠቀም ከመሠረተ ልማት ጀምሮ ኢንቨስትመንትን ለማፋጠን የሚያግዙ በርካታ ስራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛል ብለዋል። በከተማ አስተዳደሩ እስካሁን ከ4 ሺህ 500 በላይ ባለሀብቶች በተለያዩ የኢንቨስትመንት ስራዎች ተሰማርተው የሚገኙ ሲሆን፤ ብዙዎቹም በሚፈለገው መንገድ ምርት እያመረቱ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዚህም የከተማውን የኢንቨስትመንት ምርታማነት ከ42 በመቶ ወደ 54 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ተናግረው፤ በበጀት ዓመቱ መጨረሻም ምርታማነቱን ወደ 65 በመቶ ለማድረስ ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ ቀሪ ወራትም ከ2 ሺህ 200 በላይ ባለሀብቶችን ለመቀበል ዝግጅት መደረጉን ተናግረው ለዚህ ሥራም ከ3 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት መዘጋጀቱን ተናግረዋል። የኢንቨስትመንት ስራውም ወደ ሥራ ሲገባ ከ700 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ይፈጥራል ብለዋል። የሸገር ከተማ ከመመስረቷ በፊት አርሶ አደሮች በኢንቨስትመንት ምክንያት በቂ ካሳ ሳይከፈላቸው ከመኖሪያ ቤታቸው ሲፈናቀሉ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ባለው የኢንቨስትመንት ስራ ግን ለከተማው ማህበረሰብና ለአርሶ አደሩ ቅድሚያ እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። በከተማ አስተዳደሩ በኢንቨስትመንት ስራ ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች በበኩላቸው ከተማ አስተዳደሩ አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገላቸው መሆኑን ተናግረዋል። ከባለሀብቶቹ መካከል አቶ ታዲዮስ ጌታቸው፣ ከተማ አስተዳሩ ለባለሀብቶች እያደረገ ያለው ድጋፍ በጎ መሆኑን አንስተው ይህም መጠናከር እንዳለበት አመልክተዋል። ሌላው ባለሃብት አቶ በላይነህ ክንዴም የኢንቨስትመንት ስራዎቹ የቴክኖሎጂ ሽግግር እያደረጉ መሆኑንና የውጭ ምንዛሪ ወጪን በመቀነስ ለብዙ ዜጎች የስራ እድል መፍጠር መቻላቸውን አስረድተዋል።