ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ አቡዳቢ ዕለታዊ አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀመረ
Jul 15, 2025 68
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ተባበሩት አረብ ኤምሬቶች አቡዳቢ ከተማ በየቀኑ የሚደረግ አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የቦርድ ሊቀመንበር ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው የአየር መንገዱ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ በኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ኤምባሲ ምክትል የሚሲዮን መሪ ሀማድ ፋሪድና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል። የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የቦርድ ሊቀመንበር ሌተናል ጄነራል ይልማ መርዳሳ በዚሁ ወቅት፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለ80 አመታት ገደማ አፍሪካን ከመላው ዓለም እያስተሳሰረ የቆየ ግዙፍ የአቪዬሽን ማዕከል መሆኑን ገልጸዋል። በዛሬው እለትም ወደ ተባበሩት አረብ ኤምሬቶች አቡዳቢ የተጀመረው አዲስ የበረራ መስመር የሁለቱን ሀገራት ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር እንደሚሆን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው በበኩላቸው፤ አየር መንገዱ ወደ አቡዳቢ የጀመረው የመንገደኞች የበረራ አገልግሎት በአፍሪካና መካከለኛው ምስራቅ መካከል ያለውን ትስስር የሚያጎለብት ይሆናል ብለዋል። አየር መንገዱ እ.አ.አ ከ1979 ጀምሮ ወደ ዱባይ የመንገደኞች አገልግሎት በመጀመር ዛሬ ላይ በሳምንት 21 ጊዜ በረራ ያደርጋል ነው ያሉት። በዛሬው እለትም አየር መንገዱ ከረጅም ጊዜ በኋላ በአዲስ መልክ ወደ አቡዳቢ አገልግሎት መጀመሩ በመካከለኛው ምስራቅ ያለውን ተደራሽነት የሚያሰፋ ይሆናል ብለዋል። በኢትዮጵያ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ምክትል ሚሲዮን መሪ ሀማድ ፋሪድ፤ የበረራው መጀመር በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የንግድ፣ ቱሪዝም እና የባህል ልውውጥ እንደሚያሳድግ ጠቁመዋል። አየር መንገዱ ከአንድ ወር በፊት ወደ ተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ሻርጃ በሳምንት አራት ጊዜ የሚደረግ አዲስ በረራ መጀመሩ የሚታወስ ነው።
የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ከመስከረም 2018 ዓ.ም ጀምሮ ይካሔዳል - የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት
Jul 15, 2025 47
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ከመስከረም 2018 ዓ.ም ጀምሮ እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በከር ሻሌ (ዶ/ር) ገለጹ። አገልግሎቱ ዛሬ የ2018 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ የቅድመ-ዝግጅት ተግባራት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር አካሒዷል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጀቶች ቆጠራ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ስታስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በከር ሻሌ (ዶ/ር) በ2018 ዓ.ም የሚጀመረውን የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ በተመለከተ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ዋና ዳይሬክተሩ በመግለጫቸው፤ አገልግሎቱ ከ2016 ዓ.ም እስከ 2018 ዓ.ም የስታስቲክስ ልማት ፕሮግራም ቀርጾ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡ ከልማት መርሃ ግብሮቹ መካከል የኢትዮጵያ የስነ ህዝብና ጤና ጥናት፤ የኢትዮጵያ የግብርና ቆጠራ፣ ብሔራዊ የተቀናጀ የቤተሰብ ጥናትና የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከነዚህ መካከል የኢትዮጵያ የስነ ህዝብና ጤና ጥናት ማለቁን ጠቁመው፤ የኢትዮጵያ የግብርና ቆጠራ እና ብሔራዊ የተቀናጀ የቤተሰብ ጥናት በመጠናቀቅ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ በመስከረም እንደሚጀመር ገልጸው፤ በቆጠራው በመላው አገሪቷ የሚገኙ ከፍተኛ፣ መካከለኛ እና ዝቅተኛ ኢንተርፕራይዞች እንደሚካተቱ ተናግረዋል። ከቆጠራው የሚገኙ መረጃዎች በዘርፉ ለሚዘጋጁ እቅዶች፣ ፖሊሲዎች እና ስትራቴጂ ትክክለኛ ግብዓት ሆነው እንደሚያገለግሉ ጠቁመዋል፡፡ ስለሆነም በመላው አገሪቷ የሚገኙ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ቆጠራው የሚጀመራው በአዲስ ዓመት መግቢያ መሆኑን ተገንዝበው ከወዲሁ ዝግጅት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ አስተባባሪ ኮሚቴ የቅድመ ዝግጅት ስራውን ዛሬ በይፋ መጀመሩን ገልጸው፤ ስራው የስነ ጥናት ዘዴውንና ሽፋኑን እንደሚወስንም ነው የተናገሩት።
ክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፎች ስኬቶች ተመዝግበዋል - ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Jul 15, 2025 39
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 8/2017(ኢዜአ)፡- በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት ስኬታማ ውጤቶች መመዝገባቸውን የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ፡፡ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 9ኛ መደበኛ ጉባኤውን በማካሄድ ላይ ሲሆን በዛሬው ውሎው የክልሉን መንግስት የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈፃፀም ሪፖርት እና የ2018 ዕቅድ በመገምገም አፅድቋል፡፡ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ፤ ከመድረኩ በኋላ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት ማብራሪያ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ በሁሉም ዘርፎች በብዙ መመዘኛዎች ስኬታማ ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። በተለይም በምጣኔ ኃብት፣ በግብርና፣ በከተማ ልማት እንዲሁም የኢንዱስትሪና ሌሎች መስኮች የተገኙ ውጤቶችን በመዘርዘር በእንስሳት ሃብት ልማት፣ በመሠረተ ልማት ግንባታ፣ በውሃ ልማትና ተደራሽነት፣ በትምህርትና ጤና ዘርፎች በርካታ ስራዎች መሰራታቸውንና ውጤቶችም መገኘታቸውን አብራርተዋል። በክልሉ የመልካም አስተዳደር ጉዳይ በከፍተኛ ትኩረት እየተመራ ያለ መሆኑን ጠቁመው በዚህ ረገድ እንደ ሀገር የተያዘውን ግብ ለማሳካት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመፍታት ረገድም በጥናት ላይ በመመስረት በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን አንስተው በቀጣይ በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። ምክር ቤቱ ማምሻውን የክልሉን የ2018 ዓ.ም በጀት 32 ነጥብ 82 ቢሊዮን ብር ያፀደቀ ሲሆን በጀቱም ከክልሉ የውስጥ ገቢ፣ ከፌደራል መንግስት በሚሰጥ ድጎማና ከሌሎች የገቢ ምንጮች የሚሸፈን መሆኑ ተገልጿል። የምክር ቤቱ ጉባኤ ነገም ቀጥሎ የሚውል ሲሆን በቀሪ አጀንዳዎች ላይ በመወያየት ውሳኔዎችን ያስተላልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በክልሉ የግብርና ዘርፉን ምርታማነት በማሳደግ ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገው ጥረት አበረታች ነው - የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴ
Jul 15, 2025 60
ጋምቤላ ፤ሀምሌ 8 /2017 (ኢዜአ) ፡-በጋምቤላ ክልል የግብርና ዘርፉን ምርታማነት በማሳደግ ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገው ጥረት አበረታች መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት ገለፁ። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባላት በጋምቤላ ክልል ያለውን ወቅታዊ የግብርና ልማት እንቅስቃሴ ተመልክተዋል። ከጉብኝቱ በኋላ ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት የቋሚ ኮሚቴው አባላት ቡድን መሪ ወይዘሮ ሉባባ ሰይድ፤ መንግስት ለግብርናው ዘርፍ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ምርትና ምርታማነት የማሳደግ ጥረቱን አጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። በግብርና ዘርፍ ብዝሃ የምርት አማራጮችን ከማስፋት ባለፈ የግብዓት አቅርቦትን በማሟላት ምርታማነት እንዲያድግ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። በዘርፉ ልማት የጋምቤላ ክልል እምቅ አቅም ያለው በመሆኑ ልማቱን በማሳለጥ እንደ ሀገር ከተረጂነት ለመላቀቅ ለተያዘው እቅድ ትልቅ አቅም ይሆናል ሲሉም አንስተዋል። በመሆኑም በጋምቤላ ክልል የግብርና ዘርፉን ምርታማነት በማሳደግ ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገው ጥረት ተስፋ የታየበት ነው ብለዋል። የቋሚ ኮሚቴው አባል ወይዘሮ እታገኝ እሸቱ፤ በበኩላቸው በክልሉ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመላቀቅ እየተከናወነ ያለው ተግባር የሚበረታታ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ያሉ እምቅ ፀጋዎችን በአግባቡ ማልማት ከተቻለ ለሀገር የሚተርፍ ሃብት ያለበት መሆኑን በመስክ ምልከታችን አረጋግጠናል ሲሉም ገልጸዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዳግም ምላሺን፤ በዘንድሮው መኸር ከ172 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ስለመሸፈኑ አንስተው የተሻለ ምርት እንዲገኝ ቅንጅታዊ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። በምርት ዘመኑ በዘር ከተሸፈነው የእርሻ መሬት ከ5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ እቅድ መያዙንም ጠቁመዋል።
የከተማው የኮሪደር ልማት የሥራ እድል እና ከዘርፉ እውቀት እንድናገኝ አስችሎናል-ወጣቶች
Jul 15, 2025 79
ደሴ ፤ ሐምሌ 8/2017(ኢዜአ)፡-የደሴ ከተማ የኮሪደር ልማት የሥራ እድል እና ከዘርፉ የሥራ ሂደት እውቀት እንዲያገኙ ያስቻላቸው መሆኑን የከተማው ወጣቶች ገለጹ። የኮሪደር ልማቱ በተያዘለት ጊዜ እና በጥራት እንዲጠናቀቅ በርካታ ዜጎችን ወደ ሥራ በማስገባት ሥራው እንዲፋጠን እየተደረገ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ገልጿል። በልማቱ ከተሰማሩት ወጣቶች መካከል ብርሃን አስናቀ በሰጠው አስተያየት በኮሪደር ልማቱ የግንባታ ዘርፍ የሥራ እድል ተፈጥሮለት ተጠቃሚ በመሆን ላይ እንደሚገኝ ተናግሯል። በዚህም ደስተኛ እንደሆነ ጠቅሶ፤ በግንባታው ሂደትም የእውቀት ሽግግር ማድረግ እንዲችሉ ምቹ ሁኔታ እንደተፈጠረላቸው ገልጿል። በግንባታ ሥራ ካናል እና የድጋፍ ግንብ ከመስራት ባለፈ በቴራዞ ማንጠፍ፣ በእግረኛና በብስክሌት መንገድና በሌሎችም ቀለም መቀባትና ተዛማጅ ሙያዎችን ከሌሎች ባለሙያዎች ልምድ መውሰድ ችያለሁ ነው ያለው። ሌላው ወጣት መጋቢ ባዬ በበኩሉ ፤ በኮሪደር ልማቱ የሥራ እድል በማግኘቱ ከቤተሰብ ጠባቂነት ከመላቀቅ ባለፈ የእውቀት ሽግግር በማድረግ ሌሎችንም አማራጭ ሙያዎች እንድንለምድ አስችሎናል ብሏል። በዚህም ከረዳት ቴራዞ አንጣፊነት ወደ ሙሉ ባለሙያነት ማደግ በመቻሉ መደሰቱን ጠቁሞ፤ ሌሎችንም የኮንስትራክሽን ሙያዎች መልመድና መማር ችያለሁ ሲል ገለጿል። የኮሪደር ልማቱ በተያዘለት ጊዜ በጥራት እንዲጠናቀቅ በምሽት ጭምር በመስራት የድርሻዬን እየተወጣሁ ነው ያለው ወጣቱ፤ ለከተማችን መዋብና ማማር አሻራዬን ማስቀመጥ በመቻሌም እድለኛ ነኝ ብሏል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ መንግስቱ አበበ ፤ የኮሪደር ልማቱን በጥራትና ፍጥነት ለማጠናቀቅ በሶስት ተቋራጮች በርካታ የሰው ሃይል ተመድቦ እንዲፈጥን እየተደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዚህም ለሁለት ሺህ 144 ዜጎች የሥራ እድል መፍጠር መቻሉን ጠቁመው፤ የእውቅት ሽግግርም እያደረጉ የሥራ ባህል እንዲቀየር አድርጓል፣ ለሌሎች ፕሮጀክቶችም ልምድ የሚሆን ነው ብለዋል። ቀጣዩን ትውልድ ታሳቢ ተደርጎ እየተሰራ ባለው የኮሪደር ልማት የከተማውን መልካም ገጽታ ይበልጥ በማጉላት ለነዋሪዎች ምቹና ተስማሚ ከማድረግ ባለፈ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም መዳረሻም መደላድል የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል። በኮሪደር ልማቱ እየተሰራ ካለው ሁለት ኪሎ ሜትር መንገድ ውስጥ ከአንድ ነጥብ 36 ኪሎ ሜትር የሚበልጠው የአስፓልት፣ የብስክሌትና የእግረኛ መንገዶች ተጠናቀው የስማርት ፖል ተከላ ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል፡፡ ቀሪውም ሥራው በፍጥነት ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ፈጥኖ መቅረቡ የእርሻ ስራችንን በወቅቱ እንድናከናውን አስችሎናል-አርሶ አደሮች
Jul 15, 2025 88
ሰቆጣ፤ሐምሌ 8/2017(ኢዜአ)፡- ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ፈጥኖ መቅረብ በመቻሉ የእርሻ ስራቸውን በወቅቱ ማከናወን እንዲችሉ ምቹ ሁኔታ እንደተፈጠረላቸው በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ሰቆጣ ወረዳ አስተያየታቸውን የሰጡ አርሶ አደሮች ገለጹ። በብሔረሰብ አስተዳደሩ በምርት ዘመኑ 120 ሺህ 638 ሄክታር መሬትን በተለያየ የሰብል ዘር ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን የአስተዳደሩ ግብርና መምሪያ አመልክቷል። በሰቆጣ ወረዳ የሳይዳ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ደባሽ አስፋው ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ግማሽ ሄክታር የእርሻ መሬታቸውን ማዳበሪያን በመጠቀም ስንዴን በመስመር ዘርተዋል። ምርታማነታቸውን ለማሳደግ ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ፈጥኖ መቅረብ በመቻሉ የእርሻ ስራችንን በወቅቱ እንድናከናውን አስችሎናል ያሉት አርሶ አደሩ፤ከአካባቢው አርሶ አደሮች ጋር በመሆንም ስንዴን በኩታ ገጠም መዝራት መቻላቸውን አንስተዋል። በማሳቸውን ዳርቻ ላይም እርጥበትን ማቀብ የሚችል ጉድጓድ እንደሚቆፍሩ ነው የተናገሩት። አርሶ አደር ወርቁ አለሙ በበኩላቸው፥ በግማሽ ሄክታር ማሳቸው ስንዴን በመስመር መዝራታቸውን ተናግረዋል። ባለፈው የምርት ዘመን ሰብልን ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በመጠቀም መዝራት በመቻላችን ምርታማነት እንዲያድግ አስችሏል ያሉት አርሶ አደር ወርቁ፤ አሁንም በኩታ ገጠም አስተራረስ ስንዴን በመስመር መዝራታቸው የተሻለ ውጤት እንደሚጠብቁ ገልጸዋል። ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ፈጥኖ መቅረብ በመቻሉ ደግሞ የእርሻ ስራቸውን ፈጥነው ወደ ስራ እንዲገቡ ምቹ ሁኔታ እንደተፈጠረላቸው ተናግረዋል። በሰቆጣ ወረዳ እስካሁን 23 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያየ የሰብል ዘር ተሸፍኗል ያሉት ደግሞ የወረዳው ግብርና ጽህፈት ቤት የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ታምሩ አብርሃ ናቸው። በዘር ከተሸፈነው የእርሻ መሬት ውስጥም 1 ሺህ 600 ሄክታር መሬት በስንዴ፣ጤፍ ፣ማሽላና እንቁ ዳጉሳ የሰብል ዘር በኩታ ገጠም እርሻ ተሸፍኗል ብለዋል። የአርሶ አደሩ ሰብልን በመስመር መዝራት ብሎም በኩታ ገጠም የመሸፈን ልምድ እያደገ መምጣቱንም ገልጸዋል። የብሔረሰብ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ በበኩላቸው፤በምርት ዘመኑ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችል የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ መመቻቸቱን ተናግረዋል። ይህም 19ሺህ 385 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ እና 7 ሺህ 546 ኩንታል መሆኑን ጠቅሰዋል። ሃላፊው እንዳሉት፥በ2017/2018 ምርት ዘመን መታረስ ከሚችለው 120 ሺህ 638 ሄክታር መሬት በሰብል ዘር ለማልማት በእቅድ ከተያዘው ውስጥ 35 ሺህ ሄክታር ያህሉ በዘር ተሸፍኗል። በምርት ዘመኑ ከሚለማው መሬት 4 ሺህ 772 ሄክታር መሬት በስንዴ፣ጤፍ፣ማሽላና እንቁ ዳጉሳ የሰብል ዘር በኩታ ገጠም ለመሸፈን ወደ ተግባር መገባቱን ተናግረዋል።
የሀገር ውስጥ ምርቶችን መጠቀምን ሁሉም ባህል ማድረግ አለበት - የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር
Jul 14, 2025 159
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 7/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የንግድ ስርዓትን በማሳለጥ የሀገር ውስጥ ምርቶችን የመጠቀም ባህልን ማጎልበት እንደሚገባ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልሃኪም ሙሉ (ዶ/ር) ገለጹ ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ ያዘጋጀው 2ኛው ከተማ አቀፍ የኢትዮጵያን ይግዙ የንግድ ሳምንት ኤግዚቢሽንና ባዛር ተከፍቷል። ኤግዚቢሽንና ባዛሩ "የኢትዮጵያ ምርት ለብልፅግና" በሚል መሪ ሀሳብ ከዛሬ ጀምሮ እስከ ሀምሌ 11/2017 ድረስ በአዲስ አበባ ኢግዚቪሽን ማዕከል ይካሄዳል። በመርሃ-ግብሩ መክፍቻ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ ጃንጥራር አባይ፣ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልሃኪም ሙሉ (ዶ/ር)፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ ኃላፊ ሃቢባ ሲራጅ እና ሌሎችም ታድመዋል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልሃኪም ሙሉ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ 2ኛው ከተማ አቀፍ የኢትዮጵያን ይግዙ የንግድ ሳምንት ኢግዚቢሽንና ባዛር በኢትዮጵያ የሚመረቱ ምርቶችና አገልግሎቶችን የመጠቀም ባህል ለማጎልበት ነው። የኢትዮጵያን ይግዙ የንግድ ሳምንት ንቅናቄ የሀገሪቱን የንግድ ስርዓት ለማዘመን፣ ምርትና አገልግሎቶችን ተደራሽነት ለማጎልበት ያለመ መሆኑንም ተናግረዋል። የንግድ ሳምንቱ የአገር ውስጥ ምርቶችና አገልግሎቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በመሸጥና በመግዛት በኩል ለማህበረሰብ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል። የንግዱ ማህበረሰብም የንግድ ፍቃድ አውጥቶ በህጋዊ መንገድ በመስራት የዘርፉ ኢንቨስትመንት እንዲሻሻልና በዘመናዊ አሰራር እንዲካሄድ የራሱን እገዛ ሊያደርግ እንደሚገባውም ነው የገለጹት። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊ ጃንጥራር አባይ በበኩላቸው በከተማዋ የሚደረጉ የንግድ እንቅስቃሴዎች ለኢኮኖሚ እድገቱ ትልቅ ድርሻ እንደሚያበርክቱም ተናግረዋል። ኢግዚቢሽንና ባዛሩ አምራቾችንና ሸማቾችን በቀጥታ በማገናኘት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲገበያዩ ለማደረግ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንም ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሀቢባ ሲራጅ፤ ከተማ አስተዳደሩ የነዋሪውን የኑሮ ጫና ለማቃለል በከተማ ደረጃ ግብር ኃይል በማቋቋም እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎቶች ለማህበረሰቡ እንዲደርሱ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በኢግዝብሽንና ባዛሩ ላይ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የንግዱ ማህበረሰብ አባላት እንዳሉት ምርቶቻቸውን በዝግጅቱ ላይ በማቅረባቸው የተሻለ የንግድ ትስስር ለመፍጠር እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። ምርቶቻቸውን ካቀረቡት መካከልም አቶ ኤልያስ አስቻለው፤ መንግስት መሰል ባዛሮችን ማዘጋጀቱ ለምርቶቻቸው ምቹ ገበያን ከመፍጠር ባሻገር በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እንደሚያስችላቸው ገልጸዋል። ቀደም ብሎ በተካሄደው ኢግዚብሽንና ባዛር ላይ በመሳተፍ የገበያ ትስስርን በመፍጠር ምርቶቻቸውን በተሻለ መልኩ ለመሸጥ ምቹ አጋጣሚ እንደፈጠረላቸው የጠቀሱት ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ ትእግስት ተገኝ ናቸው ።
ግብርን በቴሌ ብር መክፈል ጊዜና እንግልትን ከማስቀረት ባለፈ ሀገራዊ ግዴታችንን በወቅቱ ለመወጣት እያገዘን ነው-በሲዳማ ክልል ግብር ከፋዮች
Jul 14, 2025 76
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 7/2017 (ኢዜአ)፦ ግብርን በቴሌ ብር መክፈል ጊዜያቸውን ከመቆጠብና እንግልትን ከማስቀረት ባለፈ ሀገራዊ ግዴታቸውን በወቅቱ ለመወጣት እያገዛቸው መሆኑን የሲዳማ ክልል ግብር ከፋዮች ገለጹ። የሲዳማ ክልል ገቢዎች ባለስልጣን በበኩሉ በሰባት ቀናት ውስጥ በክልሉ ከሚገኙ የደረጃ "ሐ" ግብር ከፋዮች ከ220 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ በቴክኖሎጂ የታገዘ ዘመናዊ አሰራር መዘርጋቱን አስታውቋል። በሲዳማ ክልል ከሐምሌ 1 ቀን ጀምሮ የደረጃ "ሐ" ግብር ከፋዮች በቴክኖሎጂ ታግዘው በቴሌ ብር ሃላፊነታቸውን እየተወጡ ሲሆን ዘመናዊ አሰራሩ ጊዜንና እንግልትን ከመቀነስ ባለፈ ግብራቸውን በወቅቱ በመክፈል ሀገራዊ ግዴታቸውን ለመወጣት እያገዛቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል በክልሉ የሀዋሳ ከተማ ነዋሪው ፕሮፌሰር ብርሃኑ ቦርጂ በማማከር አገልግሎት ከሚያገኙት ገቢ የሚጠበቅባቸውን ግብር በቴሌ ብር መክፈላቸው ጊዜያቸውን እንደቆጠበላቸው ገልጸዋል። ግብርን በወቅቱ መክፈል መንግስት ለሚያከናውነው የልማት ሥራ አጋዥ መሆኑን ጠቁመው፣ የግብር አሰባሰቡ መዘመኑ ግብር ከፋዩ በወቅቱ የሚጠበቅበትን ለመወጣት እያስቻለው መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ይርጋለም ከተማ የሚኖረት አቶ ምትኩ ጸጋዬ በበኩላቸው በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራር መዘርጋቱ ግብራቸውን በቴሌ ብር ለመክፈልና ጊዜያቸውን ለመቆጠብ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል፡፡ ግብር ለሃገር እድገት የሚኖረው አስተዋጽኦ የጎላ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ምትኩ የሚጠበቅባቸውን ግብር በታማኝነት እንደከፈሉና ሌሎችም ሃላፊነታቸውን በወቅቱ መወጣት እንዳለባቸው ገልጸዋል። ግብር መክፈል የዜግነት ግዴታና ለልማት የሚደረግ አስተዋጽኦ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በክልሉ የወንዶገነት ከተማ ነዋሪው አቶ ማሞ ቱላ ናቸው። በሚኖሩበት ከተማ እየተከናወነ ያለው ፈጣን የልማት እንቅስቃሴ ግዴታቸውን በወቅቱ እንዲከፍሉ ያነሳሳቸው መሆኑን ተናግረው፣ "አገልግሎቱ በቴሌ ብር መታገዙ ጊዜን ከመቆጠብ ባለፈ እንግልትን አስቀርቶልኛል" ብለዋል። የሲዳማ ክልል ገቢዎች ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተርና የደንበኞች አገልግሎት የታክስ አወሳሰንና የገቢ አሰባሰብ ዘርፍ ሃላፊ ወይዘሮ ሙላት ዮሴፍ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በክልሉ ከ35ሺህ 816 በላይ የደረጃ "ሐ" ግብር ከፋዮች ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህ ግብር ከፋዮችም በሰባት ተከታታይ ቀናት ውስጥ ከ220 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደተግባር ተገብቷል ብለዋል። በክልሉ ከሚገኙ 45 መዋቅሮች በ31ዱ የገቢ አሰባሰብ ሂደቱ በቴሌብር ታግዞ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ ዘመናዊ የግብር አሰባሰብ ሥርአት መዘርጋቱ ለግብር ከፋዮች ፈጣን አገልግሎት ለመስጠት ከማስቻሉ ባለፈ ህገወጥ ተግባራትን ለመከላከል እያገዘ ነው ብለዋል። በተጨማሪም የአንድ ማዕከል አገልግሎት በመዘርጋት ግብር ከፋዮች ንግድ ፈቃዳቸውን የሚያድሱበት እንዲሁም ሌሎች ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎቶችን የሚያገኙበት አሰራር መዘርጋቱ እንግልት ያስቀረ፣ ጊዜና ጉልበት የቆጠበ ነው ሲሉም ምክትል ዳይሬክተሯ ገልጸዋል።
አፍሪ ኤግዚም ባንክ የአፍሪካን የልማት እና ትስስር ፕሮጀክቶች መደገፉን ይቀጥላል
Jul 14, 2025 98
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 7/2017(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ኤክስፖርት እና ኢምፖርት ባንክ(አፍሪ ኤግዚም ባንክ) ለአፍሪካን የልማት እና ትስስር ፕሮጀክቶች የሚያደርገውን ድጋፍ በተጠናከረ መልኩ መደገፉን እንደሚቀጥል አስታወቀ። 47ኛው የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት እና 7ኛው የህብረቱ ቀጣናዊ ማህበረሰቦች የመንፈቅ ዓመት የጋራ የትብብር ስብሰባ በኢኳቶሪያል ጊኒ ማላቦ ተካሂዷል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ከስብሰባው ጎን ለጎን ከተሰናባቹ የአፍሪካ ኤክስፖርት እና ኢምፖርት ባንክ(አፍሪ ኤግዚም ባንክ) ተሰናባች ፕሬዝዳንት እና የቦርድ ሊቀ መንበር ፕሮፌሰር ቤኔዲክት ኦርማህ ጋር ተወያይተዋል። በውይይቱ የአፍሪካ ህብረት እና የአፍሪ ኤግዚም ባንክ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ለማጎልበትና ባንኩ ለአፍሪካ ልማት እና ትስስር የሚያደርገውን ድጋፍ የበለጠ ለማጠናከር እንደሚሰሩ ገልጸዋል። ሊቀ መንበሩ ባንኩ የኮቪድ-19 ወረርሽኝን መከላከልን ጨምሮ ለአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራትና ለኮሚሽኑ እያደረገ ያለውን ዘላቂ ድጋፍ አድንቀዋል። በተጨማሪም ሊቀ መንበሩ ከአዲሱ የባንኩ ፕሬዝዳንት ጆርጅ ኢሎምቢ(ዶ/ር) የተወያዩ ሲሆን የአፍሪካ ህብረት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግላቸው ማረጋገጣቸውን ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
በዞኑ የስራ እድል የተፈጠረላቸው ወጣቶች ምርትና አገልግሎታቸውን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እየሆኑ ነው
Jul 14, 2025 91
ነገሌ ቦረና፤ ሐምሌ 7/2017(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ቦረና ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የስራ እድል የተፈጠረላቸው ወጣቶች ምርትና አገልግሎታቸውን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኙ ተገለጸ። በዞኑ የስራ እድል ፈጠና ክህሎት ጽህፈት ቤት የስራ እድል ፈጠራ ቡድን መሪ አቶ ጎዳና ሳራ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በዞኑ ለ42ሺህ ወጣቶች የስራ እድል መመቻቸቱን ለኢዜአ ተናግረዋል። ከእነዚህም መካከል ከ10ሺህ 560 በላይ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ሰልጥነው የተመረቁ ናቸው ብለዋል፡፡ ነገሌ ቦረና ከተማ አስተዳደርን ጨምሮ አጠቃላይ በዞኑ ወደ ስራ ከገቡት ወጣቶች መካከል 15ሺህ 971 ሴቶች እንደሆኑም አንስተዋል፡፡ ወጣቶቹ ወደ ስራ የገቡት በግብርና፣ በአገልግሎትና በማኑፋክቸሪንግ ዘርፎች ሲሆን፤ ግንባታ፣ ንግድ፣ እንስሳት እርባታ፣ ማዕድን ፍለጋና ግብይት፤ የቤትና የቢሮ እቃዎች ማመርተ ሰፊውን ድርሻ ይወስዳሉ ብለዋል። ወደ ስራ ለገቡት ወጣቶች 78 ነጥብ 8 ሚሊዮን ብር ብድር በማመቻቸት ትራክተር፣ ከ10 ሄክታር በላይ የማምረቻ እና መሸጫ ቦታና 61 የመሸጫ ሱቆች ድጋፍ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡ ወደ ስራ የገቡ ወጣቶችም ምርትና አገልግሎታቸውን በብዛትና በጥራት ለገበያ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ ተጠቃሚ በመሆን ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ የነገሌ ቦረና ከተማ ነዋሪ አልዬ ዋቆ ከ3 ባልደረቦቹ ጋር በልብስ ስፌትና የአልባሳት ምርት አቅርቦት ስራ ከተሰማሩ ወጣቶች መካከል አንዱ ሲሆን፤ አልባሳቱ ባህልን ከማስተዋወቅ ባለፈ በገበያ አዋጭ በመሆኑ የተሻለ ገቢ የሚያስገኝ ተመራጭ የስራ ዘርፍ መሆኑን ገልጿል፡፡ በውጤቱም እራሳችንንና ቤተሰቦቻችንን ከመርዳት አልፈን ከንግድ ስራው የምናገኘውን ትርፍ መቆጠብ ጀምረናል ሲልም ተናግሯል፡፡ ሌላው የከተማው ነዋሪ ወጣት ቢኒያም አምሳሉና 2 ባልደረቦቹ በብረታ ብረት የስራ ዘርፍ የተሰማሩ ናቸው። ወጣት ቢኒያም በሰጠው አስተያየት፤ ምርታችንን በጥራት እያመረትን ለነገሌ ቦረና ከተማ ህዝብና ለሴክተር መስሪያ ቤቶች ጭምር እያቀረብን ነው ብሏል። አሁን ላይ ካፒታላቸው 150ሺህ ብር መድረሱን ገልጸው በቀጣይም ስራቸውን ለማስፋፋት ተጨማሪ ብድር ለመውሰድ በዝግጅት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የምግብ ዋስትና እና የምግብ ሉዓላዊነት ልዩነት አላቸው?
Jul 14, 2025 160
የምግብ ዋስትና እና የምግብ ሉዓላዊነት እሳቤዎች በዋናነት የሰው ልጆችን ምግብ የማግኘት መብት የሚያንጸባርቁ ናቸው። ይሁንና የሁለቱ ጽንሰ ሀሳቦች ፍልስፍናቸው፣ አካሄዳቸውና ትግበራቸው ለየቅል ነው። የዓለም የምግብ እና እርሻ ድርጅት(ፋኦ) የምግብ ዋስትና ማለት “ለሁሉም ሰው ሁልጊዜ በቂ፣ ደህንነቱ የተጠበቀ እና የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝ፣ የምግብ ፍላጎትና ምርጫዎቹን እንዲያሟላ ንቁና ጤናማ ህይወት እንዲኖር ማድረግ ነው” ሲል ይገልጸዋል። አቅርቦት፣ ተደራሽነት፣ መጠቀምና ደህንነት የምግብ ዋስትና ቁልፍ ምሰሶዎች መሆናቸውም ይጠቀሳል። የምግብ ዋስትና አብዛኛው ውጤቶች የሚለኩት ረሃብን መከላከል እና የተመጣጠነ ምግብ እጥረትን በመቅረፍ ነው። አካሄዱም በመንግስታት ተጽእኖ ስር የወደቀ፣ በገበያ ምርት የሚመራና ዓለም አቀፋዊነቱ ጎልቶ የሚታይ መሆኑም እንዲሁ። የምግብ ሉዓላዊነት እሳቤ የተጠነሰሰው እ.አ.አ በ1993 በቤልጂየም የተቋቋመው “LaVia Campesina” (የጢሰኞች መንገድ) የተሰኘው ዓለም አቀፍ የአርሶ አደሮች ድርጅት ነው። ድርጅቱ በዓለም ዙሪያ የሚገኙ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች፣ መሬት የሌላቸው ሰራተኞች፣ አርሶ አደሮች (በተለይም አነስተኛ እና መካከለኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮች)፣ አርብቶ አደሮች፣ የግብርና ሰራተኞች፣ ነባር ዜጎች፣ ሴት አርሶ አደሮች እና ስደተኞችን አቅፎ የያዘ ነው። የዓለም አቀፍ ንቅናቄው ዋነኛ ጭብጥ ዜጎች የምግብ ስርዓታቸውን ያለ ማንም ጣልቃ ገብነት ራሳቸው በባለቤትነት መምራት እና ማስተዳደር አለባቸው የሚል ነው። የምግብ ሉዓላዊነት ቁልፍ ጽንሰ ሀሳቦች ሀገር በቀል ቁጥጥር፣ ዘላቂ ስነ-ምህዳር መገንባትና የአርሶ አደሩን መብት ማስጠበቅ ነው። ዋነኛ ትኩረቱ በምግብ ምርት እና ስርጭት ላይ ራስ ገዝ መሆንና በራስ አቅም መወሰን እንደሆነ መረጃዎች የሚጠቁሙ ሲሆን አካሄዱ መብት እና ማህበረሰብን ያማከለ እንዲሁም ባለቤትነትን መጠበቅ መሰረት ያደረገ ነው። የምግብ ዋስትና የሚበላ በቂ ምግብ አለ ወይ? በሚል ጥያቄ ውስጥ የሚጠቀለል እሳቤ ሲሆን የምግብ ሉዓላዊነት ሰዎች ምን እንደሚበሉ እና እንዴት እንደሚበሉ መቆጣጠር ይችላሉ ወይ? የሚለው ጉዳይ ላይ ያተኩራል። የምግብ ዋስትና በምግብ የማግኘት መብት ውስጥ የመጀመሪያ ወሳኝ መንደርደሪያ ቢሆንም ያለ ምግብ ሉዓላዊነት ምሉዕ ውጤት ማግኘት እንደማይቻል የተለያዩ ጽሁፎች ያመለክታሉ። የምግብ ዋስትና የምግብ ተደራሽነትን ሊያሻሽል ቢችልም በምግብ ስርዓት ውስጥ ላሉ መዋቅራዊ ኢ-ፍትሃዊነቶች እና ዘላቂ ያልሆኑ አካሄዶች ምላሽ መስጠት አይችልም። የምግብ ሉዓላዊነት በቀጥታ መዋቅራዊ ጉዳዮችን ይነካል። ሀገራት የምግብ ምርት እና ስርጭትን ጨምሮ አጠቃላይ የምግብ ስርዓትን ሀገራት በራሳቸው እንዲቆጣጠሩ የሚሟገት እሳቤ እና መንገድ ነው። የስነ ምግብ ባለሙያዎች የምግብ ሉዓላዊነት የሚያረጋግጥ ሀገር በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ መንገድ የምግብ ዋስትና የማረጋገጥን ጥያቄ እንደሚመልስ ይገልጻሉ። ኢትዮጵያም በምግብ ስርዓት ሽግግር ከምርት እስከ ተጠቃሚ ባለው ሰንሰለት በራሷ በመቆጣጠር የምግብ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ እየሰራች ትገኛለች። የዜጎችን የምግብ ፍላጎት በራስ የምርት አቅም የመሙላት ስራ በማከወን ከውጭ ሀገራት ምርት ጠባቂነት ለመላቀቅ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ውጤት እያስገኙ ነው። ኢትዮጵያ በስንዴ ልማት ከልመና ወጥታ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ውጭ ገበያ መላክ መጀመሯ ታሪካዊ ድል ሲሆን ከውጭ የኢኮኖሚ ጥገኝነት በመላቀቅ የዜጎችን የምግብ ሉዓላዊነት ለማስከበር በስንዴ ልማት የተመዘገበውን ስኬት በሌሎች የግብርና መስኮች ለመድገም በመሰራት ላይ ይገኛል። በሩዝ፣ አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ ሻይ ቅጠልና ሌሎች የተለያዩ ሰብሎች ላይ እየተከናወነ ያለው ስራ ተጨባጭ ውጤቶች እያስገኘ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በምግብ ዋስትናና በተመጣጠነ የምግብ አቅርቦት ላሳዩት ርዕይ፣ የአመራር ቁርጠኝነት ከዓለም የምግብ እና የእርሻ ድርጅት(ፋኦ) የአግሪኮላ ሜዳልያ በጥር ወር 2016 ዓ.ም ያበረከተው ሽልማት ለምግብ ሉዓላዊነት ጥረት የተሰጠ እውቅና ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የኢትዮጵያ መንግስት ረሃብን ሙሉ በሙሉ ለማስቀረት እና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በዚህም ብሔራዊ ብልጽግናን እውን ለማድረግ እየሰራ መሆኑን በሽልማቱ ወቅት ገልጸው ነበር። ኢትዮጵያ በርካታ ያልተነኩ ጥሬ ሃብቶች፣ ተስማሚ የአየር ንብረትና ለስራ ትጉ የሆነ ወጣት እንዳላትና እነዚህን ሃብቶች ታሳቢ በማድረግ ሀገሪቱን በልማት ወደ ፊት ማራመድ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአንድ ወቅት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስከበር ዋጋ እንደከፈልን ሁሉ ከምግብ ጥገኝነት ለመላቀቅ በትጋት መስራት እንደሚገባ ተናግረው ነበር። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሰጡት ማብራሪያ ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነት ማግኘት አለባት፤ አምርታ መብላት ያልቻለች ሀገር ብሔራዊ ጥቅሞቿን ለማረጋገጥ ትቸገራለች በሚል የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ግብ ይዘን ሰርተናል ብለዋል። በዚህ እሳቤ 23 ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ከሴፍቲኔት ተረጂነት ነጻ መውጣታቸውን ጠቁመው ኢትዮጵያ ሙሉ ለሙሉ የምግብ ሉዓላዊነቷን ያረጋገጠች ሀገር ማድረግ አለብን ለዚህም ሰፊ የሚታረስ መሬት እለን ማለታቸው ይታወሳል። የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ(ዶ/ር) በተመሳሳይ ኢትዮጵያ በዓድዋ ጦርነት ያስመዘገበችውን አኩሪ ድል በዘመናዊ ግብርና የዜጎችን የምግብ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ እንደግመዋለን ሲሉ ገልጸው ነበር። የምግብ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥ ሀገራዊ ትልም ኢትዮጵያን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት በማሸጋገር ለተሟላ ሀገራዊ ክብር፣ ነጻነት እና ሉዓላዊነት የሚያሸጋግር መልካም ጅማሮ ነው። ሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ በኢትዮጵያ እና በጣልያን በጋራ አዘጋጅነት ከሐምሌ 20 እስከ 22 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል። ኢትዮጵያ በስርዓት ምግብ ትራንስፎርሜሽን፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥና በግብርናው ዘርፍ ባደረጋቻቸው ሀገር በቀል ሪፎርሞች ያስመዘገበቻቸው ውጤቶች ጉባኤውን እንድታስተናግድ ለመመረጥ ምክንያቶች ናቸው። ኢትዮጵያ በስርዓተ ምግብ ለውጥ ውስጥ እየተወጣች ያለው የመሪነት ሚና እና በማደግ ላይ ከሚገኙ ሀገራት በስርዓተ ምግብ ተምሳሌት የሆነች ሀገር መሆኗ ተመድ ዓለም አቀፉን ከፍተኛ ጉባኤ በኢትዮጵያ እንዲያደርግ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል። በጉባኤው ላይ ኢትዮጵያ የስርዓተ ምግብ ሽግግርን ለማሳካት እያከናወነች ባለው ተግባር ዙሪያ ተሞክሮዋን ለዓለም ማህበረሰብ የማሳወቅ ስራ ታከናውናለች።
ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 4ሺህ 700 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ ገብቷል - ቢሮው
Jul 14, 2025 114
አሶሳ፤ ሐምሌ 7/2017(ኢዜአ)፦ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 4ሺህ 700 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ መግባቱን የክልሉ ማዕድን ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ አድማሱ ሞርካ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደተናገሩት በ2017 በጀት ዓመት 1ሺህ 500 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ ለማስገባት ታቅዶ ሲሰራ ቆይቷል። በቅንጅት በተከናወኑ ተግባራት ከዕቅዱ በላይ 4ሺህ 700 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ ገቢ መደረጉን ገልጸዋል። ከዕቅዱ በላይ የተከናወነበት ምክንያትም መንግስት ለወርቅ አቅራቢዎች ያደረገው ማበረታቻ እና ህገ-ወጥ ግብይት መቀነስ ትልቅ አስተዋፅኦ ነበራቸው ብለዋል። በተለይም በሀገር አቀፍ ደረጃ በተተገበረው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ዘርፉ እንዲነቃቃና አምራቹ ተጠቃሚ እንዲሆን ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ጠቅሰዋል። በክልሉ የተመረተው ወርቅ በአነስተኛና ባህላዊ ወርቅ አምራቾች መሆኑን ገልጸው፤ ይህም የህብረተሰቡን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት አሳድጓል ነው ያሉት። ከወርቅ በተጨማሪ የድንጋይ ከሰልና እምነበረድ በስፋት እየተመረተ መሆኑን ጠቅሰው በክልሉ የሚገኙ የማዕድን ሀብቶች ጥቅም ላይ እንዲውሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል። ከማዕድን ምርቱ 49 ሚሊዮን ብር መሰበሰቡንም ነው አቶ አድማሱ ጨምረው የተናገሩት። በቀጣይ ትላልቅ ካምፓኒዎችን በመጋበዝ በክልሉ በማዕድን ዘርፍ ለማሰማራት ዝግጅት መጠናቀቁንም አስታውቀዋል።
በአዲሱ በጀት አመት ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ተጠናክሮ ይቀጥላል- የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል
Jul 13, 2025 145
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦በ2018 በጀት አመት ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ተናገሩ። የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ የኢንተርፕራይዞች ምስረታ እና የሰልጣኞች ምዝገባ በኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት ተግባራዊ የማድረግ ሥራ እንደሚቀጥልም ሚኒስትሯ ገልጸዋል። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የዘርፉ የክልልና ከተማ አስተዳደር አመራሮች የኢንተርፕርነርሺፕ ስልጠና እና ዓመታዊ የዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚልን ጨምሮ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የተጠሪ ተቋማት ኃላፊዎች፣ የክልልና የከተማ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊዎች፣ የፖሊ ቴክኒክ ኮሌጅ ዲኖች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በመድረኩ እንደተናገሩት፤ ባለፉት አመታት በተቋም ግንባታ፣ በክህሎት ልማት፣ በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በአሠሪና ሠራተኛ አበረታች ተግባራት ተከናውነዋል። የተቋም ግንባታው ሀገር የጀመረችውን ሁለንተናዊ ብልፅግና ለማረጋገጥ በሚችል መልኩ መገንባቱን ጠቅሰው፤ የአሠራር ሥራዓቶችን የማሻሻል እና በቴክኖሎጂ የማዘመን ሥራም በትኩረት መሠራቱን ገልጸዋል። ይህም በ2018 በጀት አመት ይበልጥ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነው ሚኒስትሯ ያስታወቁት። በክህሎት ልማት ረገድም በተጠናቀቀው በጀት አመት አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ጠቅሰው፤ የሰው ሀብት ልማት ሥራም ገበያ እና ፍላጎትን መሠረት በማድረግ መሰራቱን ተናግረዋል። የሥራ እድል ፈጠራ ቁጥር ሪፖርት ጥራቱን የጠበቀ ለማድረግም የኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት ተግባራዊ መደረጉን ገልጸዋል። ህጋዊ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪትን ተግባራዊ ለማድረግ፣ ለኢንተርፕራይዞች የገበያ ትስስር ለመፍጠርና ፋይናንስን ጨምሮ አስፈላጊ መንግስታዊ ድጋፎችን ለማቅረብ የሚያስችል እንደሆነም ተናግረዋል። በ2018 በጀት አመት ሁሉም የዘርፉ ተቋማት የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ የኢንተርፕራይዞች ምስረታ እና የሰልጣኞች ምዝገባ በኢትዮጵያ የሥራ ገበያ መረጃ ሥርዓት የማካሄድ ሥራን አጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ሚኒስትሯ አስገንዝበዋል። በሀገር ውስጥ፣ በውጭ ሀገር እና በርቀት ሥራ ዕድል ፈጠራ አበረታች ስራዎች መሰራቱን ጠቅሰው፤ በአዲሱ በጀት አመትም የበለጠ ስኬት ለማስመዝገብ ርብርብ እንደሚደረግ አመላክተዋል።
በዞኑ የህብረት ስራ ማህበራትን አቅም በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው
Jul 13, 2025 80
ደብረማርቆስ ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን የህብረት ስራ ማህበራትን አቅም በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑ ተገለፀ። የዞኑ ግብርና መምሪያ 17 የእርሻ ትራክተሮችና ኮምባይነሮችን ለሁለገብ የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበራትና ባለሀብቶች ዛሬ አስረክቧል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኑርልኝ ብርሃኑ እንዳሉት በዞኑ የህብረት ስራ ማህበራትን አቅም በማጠናከር ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው። የምርታማነት ማደግ የአርሶ አደሩን የኑሮ ደረጃ ከማሻሻል ባለፈ ገበያን በማረጋጋት የዋጋ ንረትን በመቀነስ ረገድ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። የዞኑን የምርታማነት አሁን ካለበት ለማሳደግ የሜካናይዜሽን ግብርናን ማስፋፋትና ተደራሽ ማድረግ የህልውና ጉዳይ ሊሆን ይገባል ያሉት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበበ መኮንን ናቸው። ለዚህም የክልሉ መንግስት ባደረገው ድጎማ ዘጠኝ ትራክተሮችና ስድስት ኮምባይነሮችን ለሁለገብ የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበራት ድጋፍ ማድረግ እንደቻለም ተናግረዋል። በተጨማሪም በረጅም ጊዜ ክፍያ ለሁለት ባለሀብቶች ሁለት ትራክተሮች ቀርበው ርክክብ መደረጉን ገልጸዋል። የክልሉ ህብረት ስራ ማህበራት ኤጀንሲ አማካሪ አቶ ሃይለ ልኡል ተስፋ በበኩላቸው የሜካናይዜሽን ግብርና ተደራሽነት እንዲሰፋ አልሚ ባለሃብቶችን ከቀረጥ ነጻ እንዲያስገቡ እና ብድር እንዲያገኙ የሚደረገው ጥረት እንዲጠናከር ጥሪ አቅርበዋል። በተጨማሪም ሁለገብ የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበራት በራሳቸው አቅም የሜካናይዜሽን እርሻን እንዲያስፋፉ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግላቸውም ገልፀዋል። በእነማይ ወረዳ የልምየት የገበሬዎች ህብረት ስራ ማህበር አባል አርሶ አደር ብርቄ ጸጋዬ እንዳሉት ''የሜካናይዜሽን አቅርቦት ድጋፍ መደረጉ በስራችን እንድንበረታ የሚያደርግ ነው'' ብለዋል። ከዚህ ቀደም ሜካናይዜሽን ባለመኖሩ በባህላዊ አስተራረስና የምርት አሰባሰብ ጊዜያቸውን ያባክኑ እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ግን በአካባቢው የሜካናይዜሽን እርሻ መጀመሩ የአርሶ አደሩን ችግር ያቃልላል የሚል ተስፋ ማሳደሩንም አርሶ አደር ብርቄ ተናግረዋል። በዞኑ ለምርት ዘመኑ ከ642 ሺህ ሄክታር በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን በዚህም ከ25 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚገኝም ተገልጿል። በምስራቅ ጎጃም ዞን በሰብል ከሚሸፈነው መሬት 58 በመቶ የሚሆነው በትራክተር ለመታረስ ምቹ መሆኑም ከዞኑ ግብርና መምሪያ የተገኘው መረጃ ያስረዳል።
ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራቾች በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት እያሳዩ ነው
Jul 13, 2025 226
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራችና ሻጭ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ምርታቸውን ለማቅረብና በዘርፉ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ፍላጎት እያሳዩ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን ገለፁ። በየዓመቱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን የሚገጣጥሙና ለሽያጭ የሚያቀርቡ ተቋማት ቁጥር እያደገ መምጣቱንም ገልፀዋል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን ለኢዜአ እንደገለጹት በአገሪቱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለማስፋፋትና በዘርፉ ያለውን ኢንቨስትመንት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው። የነዳጅ ኃይል ጥገኝነት ለመቀነስና የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ዘርፉን አገሪቱ ካላት እምቅ የታዳሽ ሃይል ሀብት ተጠቃሚ ለማድረግ አበረታች ስራዎች መጀመራቸውን ተናግረዋል። ሀገር አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከሪካሪዎች ስትራቴጂን ተግባር ላይ በማዋል ተግባራዊነቱን ለማፋጠንና ኢንቨስትመንቱን ሳቢ ለማድረግ የሚረዱ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። መንግስት በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ የመቀየር እንዲሁም የነዳጅ አጠቃቀምንና ብክለትን በሚቀንሱ ቴክኖሎጂዎች ላይ የሚሰሩ ስራዎችን እያበረታታ መሆኑንም አስታውቀዋል። በነዳጅ የሚሰሩ የቤት አውቶሞቢሎች ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ እገዳ መጣሉን አንስተው በአለም ገበያ ተደራሽ ያልሆኑ ከባድ ተሽከርካሪዎችና መሳሪያዎች በእገዳው አለመካተታቸውን ጠቅሰዋል። በቅርቡ ከሁለት እግር ጀምሮ እስከ ከተማ አውቶብስ ያሉና በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን በሀገር ውስጥ መገጣጠም መከልከሉን አንስተዋል። በዘርፉ ለተሰማሩ ባለሃብቶች የተለያዩ ማበረታቻዎች በፖሊሲ፣ ስትራቴጂና በመመሪያ ተደግፈው ተግባራዊ በመደረጋቸው በርካታ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል። በአሁኑ ወቅት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቁጥር ከ115 ሺህ በላይ እንዲሁም የኤሌክትሪክ ተሽከሪካሪ መገጣጠሚያ ድርጅቶች ቁጥር ከ15 በላይ መድረሱን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ለዘርፉ የሰጠችውን ትኩረት ተከትሎ አሁን ላይ በርካታ ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ አምራቾችና ሻጮች በዘርፉ በኢንቨስትመንት ለመሰማራት ሰፊ ፍላጎት እያሳዩ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በአሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚሰጥ የከተማ የብዙሃን ትራንስፖርት አገልግሎትን ለማስፋፋት የሚረዱ ስራዎች በመንግስትና በግል አጋርነት መጀመራቸውን ጠቅሰዋል። በአዲስ አበባ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ባትሪ መሙያ ቋሚ ጣቢያዎች ቁጥር ከ90 እንደማይበልጥ አንስተው ይህንን ለማሳደግ የመንግስት የልማት ድርጅቶችና የግል ባለሀብቶች በዘርፉ እንዲሰማሩ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ መንግሥት ተግባራዊ ያደረጋቸው የኢኮኖሚ ሪፎርሞች የህንድ ባለኃብቶች በኢትዮጵያ ያላቸው ተሳትፎ እንዲጨምር ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው
Jul 13, 2025 106
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ መንግሥት ተግባራዊ ያደረጋቸው የኢኮኖሚ ሪፎርሞች የህንድ ባለኃብቶች በኢትዮጵያ ያላቸው ተሳትፎ እንዲጨምር ምቹ ሁኔታ የፈጠሩ ናቸው ሲሉ በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ገለጹ። የኢኮኖሚ ሪፎርሙ መንግሥት የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ለማሳደግ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑንም አምባሳደሩ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በኢትዮጵያ በተለያዩ መስኮች ተግባራዊ የተደረጉ የኢኮኖሚ ሪፎርሞች በህንድ እና በኢትዮጵያ መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግሩ ናቸው። መንግስት ከወሰዳቸው የሪፎርም እርምጃዎች መካከል የውጭ ምንዛሬ ተመን በገበያው እንዲወሰን መደረጉ፣ የውጭ አገር ዜጎች የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለቤት መሆን የሚችሉበት አዋጅ መጽደቁ የውጭ ባለኃብቶችን ተሳትፎ የሚያሳድግ ትልቅ እርምጃዎች ናቸው ብለዋል። ከዚህ ቀደም ለውጭ ባለኃብቶች ዝግ የነበሩ የኢኮኖሚ መስኮች ክፍት መደረጋቸው የውጭ ባለኃብቶች በኢትዮጵያ እንዲሰማሩ መፈቀዱ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን የሚያበረታታ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የህንድ ኩባንያዎችም በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት ማሳየታቸውን ጠቁመው፤ በማዕድን፣ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በባንክና ፋይናንስ፣ የካፒታል ገበያ በርካታ ቁጥር ያላቸው የህንድ ባለኃብቶች ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎት እንዳላቸው ጠቁመዋል። በግብርናው መስክም ኢትዮጵያ ውጤታማ ለመሆን የሚያስችሉ እምቅ አቅም እንዳላት የገለጹት አምባሳደሩ፤ ሰፊ የሚታረስ መሬት፣ የውኃ ኃብት የሰው ኃይልና ሌሎች የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት የሚስቡ አቅሞች መሆናቸውን ተናግረዋል። የህንድ ባለኃብቶችም በግብርናው ዘርፍ በሰብል ልማት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በአበባ ልማት እንዲሁም ለመድሃኒት ምርት ግብዓት የሚውሉ ተክሎች ልማት ላይ የመሳተፍ ፍላጎት እንዳላቸውም አንስተዋል። በንግድና በኢንቨስትመንት በኩልም በአገራቱ መካከል ያለውን ግንኙነት ወደ ስትራቴጂያዊ አጋርነት ማሳደግ እንደሚያስፈልግ ጠቁመው፤ በዚህም ላይ እየተሰራ ነው ብለዋል። በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የንግድ ልውውጥ ለማሳለጥ የሚረዳ የጋራ የንግድ ኮሚሽን መቋቋሙን ገልጸው፤ ኮሚሽኑ ግንኙነቱን በሚያሳድጉ ጉዳዮች ላይ እየተወያየ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ በየዘርፉ ያሉ የኢንቨስትመንት አማራጮች ላይ ከሚመለከታቸው አካላት ተገቢውን ገለጻ እያገኘን ነው ያሉት አምባሳደሩ በአገራቱ መካከል ያለው ግንኙነት እየተጠናከረ መምጣቱን አብራርተዋል። የብሪክስ የትብብር ማዕቀፍም አገራቱ ግንኙነታቸውን ይበልጥ እንዲያሳድጉ ዕድል መፍጠሩን አስረድተዋል።
በመዲናዋ በከተማ ግብርና ከ159 ሺህ በላይ አዳዲስ ተጠቃሚዎች ወደ ስራ ገብተዋል
Jul 13, 2025 82
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦በ2017 በጀት ዓመት ከ159 ሺህ በላይ አዳዲስ ተጠቃሚዎች ወደከተማ ግብርና ስራ መግባታቸውን የአዲስ አበባ የአርሶ አደርና ከተማ ግብርና ልማት ኮሚሽን ገለጸ። የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር መሰለ አንሸቦ ለኢዜአ እንደገለጹት የከተማ ግብርና በተለይ የሌማት ትሩፋት መርኃ ግብር ከጊዜ ወደ ጊዜ ውጤታማነቱ እየጨመረ መጥቷል። ኮሚሽኑ በበጀት አመቱ በዘርፉ ለተሰማሩ ነዋሪዎች አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ማድረጉን ገልፀው፤ ቀደም ብለው ወደ ዘርፉ የገቡትን አጠናክሮ የማስቀጠልና አዳዲስ ስራ ጀማሪዎችን ወደ ስራ የማስገባት ስራ በትኩረት መስራቱን አንስተዋል። በኅብረተሰቡ ዘንድ በትንሽ ሥፍራ የከተማ ግብርናን ተግባራዊ በማድረግ ከራስ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ትርፋማ መሆን እንደሚቻል የግንዛቤ ፈጠራ ስራ በስፋት መሰራቱንም ተናግረዋል። በዚህም ካሁን ቀደም በዘርፉ የተሰማሩትን ከማስቀጠል ባለፈ በበጀት ዓመቱ 159 ሺህ 686 አዳዲስ ዜጎችን ወደ ዘርፉ ማስገባት መቻሉን ጠቅሰዋል። በሌላ በኩል በመዲናዋ የሚገኙ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ 2 ሺህ 565 ተቋማት ወደ ግብርና ስራ እንዲገቡ መደረጉን ጠቁመዋል። ከነዚህም መካከል 1ኛ እና 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች፣ ጤና ጣቢያዎች እና ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት እንደሚገኙበት ጠቅሰው፤ ሰራተኞች ምርቶችን በተመጣጣኛ ዋጋ ገዝተው እንዲጠቀሙ እድል መፍጠሩንም ገልጸዋል። የከተማ ግብርና ልማት በገበያ የምርት እጥረት እንዳይኖር ከማድረግ ባሻገር በበጀት አመቱ ለ9 ሺህ 526 ወጣቶች የስራ እድል መፍጠሩን ጨምረው ገልፀዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር፣ በእንስሳት እርባታ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ምርት ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የመዲናዋ ነዋሪዎች የተናገሩት። በዘርፉ ከተሰማሩት መካከል ወጣት ነብዩ ማሞ በግል ተቋም ተቀጥሮ ይሰራ እንደነበረ ገለፆ፤ የከብት እርባታ ስራ ከጀመረ ወዲህ ግን ትርፋማ መሆኑን ተናግሯል። በዚህም በውስን በጎችና በአንድ ላም የጀመረው ስራ አሁን ላይ የተሻለ ውጤት እያስገኘለትና ከራሱ አልፎ ለሌሎች ወጣቶች የስራ እድል ለመፍጠር እንዳስቻለው ጠቅሷል። በወተት ላም እርባታ፣ በዶሮ እርባታና እንቁላል ምርት ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን የሚገልጹት ደግሞ አቶ ፋሲል አዘነ የተባሉ የከተማዋ ነዋሪ ናቸው። አቶ ፋሲል ከ3 አመት በፊት ስራውን ሲጀምሩ ከ6 ላሞች በቀን 125 ሊትር ወተት ለገበያ ሲያቀርቡ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ላይ ወደ 57 ላሞች በማርባት በቀን 250 ሊትር ወተት ለገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። አሁን ላይ ለበርካታ ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር መቻላቸውንም ነው የተናገሩት ።
የሀገር ውስጥ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎትን በጥራትም በስፋትም ለማሻሻል ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተከናወኑ ነው - የኢትዮጵያ አየር መንገድ
Jul 13, 2025 96
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ የሀገር ውስጥ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎትን በጥራትም በስፋትም ለማሻሻል ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ። የኮምቦልቻ ተርሚናል በተያዘው በሐምሌ ወር መጨረሻ እንደሚመረቅ ተመላክቷል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በኢትዮጵያ ትልቁን የአየር ትራንስፖርት የሚሰጠው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ብቻ መሆኑን ገልጸዋል። አሁን ላይ በ22 ከተሞች የበረራ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም በአፍሪካ ትልቅ አገልግሎት መሆኑን ጠቁመዋል። አገልግሎቱ አሁንም በቂ አለመሆኑን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈፃሚው ደረጃውን በጥራትም ሆነ በስፋት ለማሳደግ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከእነዚህም መካከል መንገደኞች የሚስተናገዱባቸው ተርሚናሎች ደረጃቸውን የጠበቁ በማድረግ ረገድ በበርካታ ኤርፖርቶች ከፍተኛ ስራ መሰራቱን አስታውቀዋል። በተጨማሪም የአዳዲስ የተርሚናሎች ግንባታ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው የኮምቦልቻ ተርሚናል ግንባታ ስራም በተያዘው የሐምሌ ወር መጨረሻ እንደሚመረቅ ተናግረዋል። በተጨማሪም በሽሬ፣ ነቀምት እና ደምቢዶሎ አዳዲስ ተርሚናሎች ለመገንባት እቅድ መያዙን ጠቁመዋል። ነባር የአውሮፕላን መንደርደሪያዎችን በማደስ ትልልቅ አውሮፕላኖችን ማስተናገድ በሚችሉበት ደረጃ ከፍ የማድረግ ስራዎችም እየተሰሩ መሆኑን አመላክተዋል። ምንም ኤርፖርቶች ባልነበሩባቸው አካባቢዎችም ስድስት ኤርፖርቶች እየተገነቡ መሆናቸውንም ነው ዋና ሥራ አስፈፃሚው የገለጹት። ከእነዚህም መካከል የያቤሎ ኤርፖርት በነሐሴ ወር እንደሚመረቅ ተናግረዋል። አየር መንገዱ የሀገር ውስጥ የአየር ትራንስፖርት አገልግሎትን በጥራትም ሆነ በስፋት ለማሻሻል ዘርፈ ብዙ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ወጪን በራስ አቅም የመሸፈን ሂደቱን አሳድጓል
Jul 13, 2025 92
አሶሳ፤ ሐምሌ 6/2017 (ኢዜአ)፦በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በ2017 በጀት ዓመት በቅንጅት በተሰበሰበ ገቢ ወጪን በራስ የመሸፈን ሂደቱን በማሳደግ ላይ መሆኑን የክልሉ ገቢዎች ባለስልጣን አስታወቀ። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ተፈሪ አበበ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ በበጀት ዓመቱ 4 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ዕቅድ ተይዞ ሲሰራ ቆይቷል። በበጀት ዓመቱን በተቀናጀ አኳኋን በተሰራው ሥራም ከእቅድ በላይ አምስት ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ተችሏል ብለዋል። ከተለያዩ ተቋማት ጋር የነበረው ቅንጅታዊ አሰራር መጠናከር፣ ዘመናዊ የታክስ አስተዳደር ስርዓት መስፈን እና የህግ አሰራሮች ላይ ማሻሻያ መደረጉ የላቀ አፈጻጸም እንዲመዘገብ አድርጓል ብለዋል። ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ46 በመቶ ብልጫ እንዳለው አቶ ተፈሪ አስታውቀዋል። ክልሉ የራሱን ወጪ የመሸፈን አቅሙን ለማሳደግ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው በዚህ ዓመት የራሱን ወጪ የመሸፈን አቅሙ ወደ 60 በመቶ ከፍ ማለቱን ተናግረዋል። ግብር ከፋዩ ግብርን በወቅቱ የመክፈል እና የግብርን አስፈላጊነት እየተገነዘበ በመሆኑ የታክስ ማጭበርበር እና ስወራ እየቀነሰ መምጣቱን አመላክተዋል። ክልሉ ካለው የገቢ አማራጭ አንፃር መሰብሰብ የሚገባውን ገቢ አላገኘም ያሉት አቶ ተፈሪ ተጨማሪ የገቢ አማራጮች ላይ ጥናት እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።
በዘንድሮ የመኸር ወቅት እስከ አሁን 7 ሚሊየን ሄክታር መሬት በዘር ተሸፍኗል
Jul 13, 2025 67
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦በ2017/18 የመኸር ወቅት እስከ አሁን 7 ሚሊየን ሄክታር መሬት በዘር መሸፈኑን የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ገለጹ። የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የሚያስችል ስራ እየተከናወነ ይገኛል። በግብርናው ዘርፍ በመኸር፣ በበልግ እንዲሁም በመስኖ ልማት ስራዎች ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ ሥራዎች አመርቂ ውጤቶች መመዝገቡን አስታውሰዋል። በዚህ ዓመት በመላ አገሪቱ 21 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በመኸር እርሻ በተለያዩ ሰብሎች ዘር እንደሚሸፈን ገልጸዋል። አሁን ላይ በከፍተኛ ሁኔታ የዘር ስራ የሚከናወንበት በመሆኑ እንደ በቆሎ ያሉ የአገዳ ሰብሎች ቀድሞ መዘራታቸውን ጠቁመው፣ ጤፍ፣ ስንዴ፣ ገብስና ሌሎች እንደየ አካባቢው ሥነ-ምህዳር እየተዘሩ መሆኑን ተናግረዋል። ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም እና ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ በመፍጠር ጭምር በመሰራቱ በዚህ ዓመት የተሻለ ምርት ይጠበቃል ብለዋል። ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ የሚያችሉ የአፈር ማዳበሪያ፣ የምርጥ ዘር እና የተለያዩ ግብዓቶች ለአርሶ አደሩ በወቅቱ እንዲደርሱ መደረጉንም ተናግረዋል። የመኸር የእርሻ ጊዜ ለኢትዮጵያ ትልቁ የምርት ጊዜ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሩ፤ በዓመቱ በአጠቃላይ ከሚመረተው ምርት 70 በመቶ የሚሆነው በዚሁ ወቅት የሚለማ መሆኑንም ተናግረዋል። ሚኒስትሩ እንደገለጹት ዘንድሮ 13 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በኩታ ገጠም የሚለማ ሲሆን ይህም ከባለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር እድገት ማሳየቱን ገልጸዋል። አርሶ አደሩ በኩታ ገጠም በሚሰራበት ወቅት ምርታማነቱ የበለጠ እንደሚጨምር አስታውሰው ይህም የበለጠ መጠናከር እንዳለበት አስታውቀዋል። 6 ሚሊየን ሄክታር መሬት በመካናይዜሽን የታረሰ መሆኑን ገልጸው ይህም ከባለፈው በ1 ሚሊየን ሄክታር መሬት ብልጫ እንዳለው ጠቅሰዋል። የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር ትልቁ ለውጥ የአርሶ አደሮች የቴክኖሎጂን መጠቀም ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ በመምጣቱ መሆኑንም ተናግረዋል። በመኸር ወቅት 21 ሚሊየን ሄክታር መሬት በሰብል በመሸፈን ከ659 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ ይገኛል።