ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ዘላቂ ሰላም ከማስፈን በተጓዳኝ የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የመሰረተ ልማት ስራዎች ተጠናክረው ቀጥለዋል -የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)
Dec 29, 2025 21
ባህርዳር፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም ከማስፈን በተጓዳኝ የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለጹ። በክልሉ የመሰረተ ልማት ክላስተር የ5 ወራት የእቅድ አፈፃፀም ግምገማ በባህርዳር ከተማ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)፤ ከምንም በላይ በክልሉ አስተማማኝ ሰላምና መረጋጋት በመፍጠር ሂደት መንግስት በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም በሁሉም አካባቢዎች ሰላምን የማጽናትና የልማት ስራዎችን የማስቀጠል ስራ በተቀናጀ መልኩ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በፌዴራልና በክልሉ መንግስት በጀት በተለያዩ አካባቢዎች የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች በጥራትና በፍጥነት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል። በግንባታ ላይ የሚገኙ ፕሮጀክቶች ጥራታቸው ተጠብቆ በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ ጠንካራ የክትትልና ድጋፍ ስራዎች ስለመኖራቸውም ገልጸዋል። የአማራ ክልል መንገድ፣ ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ቢሮ ኃላፊ ጋሻው አወቀ (ዶ/ር) በበኩላቸው ባለፉት አምስት ወራት 389 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ ለመገንባት ታቅዶ ከ70 በመቶ በላይ መፈጸም መቻሉን አስረድተዋል። በጥገና በኩልም ሰባት ሺህ 100 ኪሎ ሜትር መንገድ በመጠገን ለአገልግሎት ማብቃት መቻሉን አስረድተዋል። የክልሉን ህዝብ የንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ተደራሽ ለማድረግ መሰራቱን የተናገሩት ደግሞ የአማራ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ ዳኝነት ፈንታ (ዶ/ር) ናቸው። ባለፉት አምስት ወራትም በጥናትና ዲዛይን የሚገነቡ ፕሮጀክቶችን በመለየት፣ በጨረታና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ በማተኮር መሰራቱንም አስረድተዋል። በክላስተሩ የእቅድ አፈፃፀም ግምገማው ላይ የክልሉ ባለድርሻ ተቋማትና የፌደራል መስሪያ ቤቶች ኃላፊዎች ተሳትፈዋል።
የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የኢንዱስትሪ የምርት ተወዳዳሪነትን ለማሳለጥ ጉልህ ፋይዳ ይኖረዋል
Dec 29, 2025 48
አዲስ አበባ፤ ታኅሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ የአምራች ኢንዱስትሪ የምርት ጥራትና ተወዳዳሪነትን ለማሳለጥ ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ማጠናቀቂያና የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ማስጀመሪያ በአዲስ ኢንተርናሽናል ኮንቬንሽን ማዕከል መካሄዱ ይታወቃል። በዚሁ ወቅትም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ተደራሽነትን ማስፋት፣ ለዜጎች እኩል ዕድል መፍጠር፣ የዜጎችና ተቋማትን መተማመን ማጎልበት ቁልፍ ትልሞች መሆናቸውን አጽንኦት ሰጥተዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ቁልፍ ትልሞችም የሕዝብ ዲጂታል መሠረተ ልማቶችን በማስፋት የዜጎችን የዕለት ከዕለት ኑሮ በሰው ተኮር ዲጂታል ሥርዓት ማሻሻል እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር አቶ መላኩ አለበል ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ መነሻነት የአምራች ኢንዱስትሪ ምርታማነትን ማዘመን የሚያስችል መሰረት ተጥሏል ብለዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂም በዘመናዊ የቴክኖሎጂ ሥርዓት የታገዘ ተወዳዳሪ የአምራች ኢንዱስትሪ ምርታማነት አቅም ለመገንባት ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው አንስተዋል። በቀጣይም በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ መነሻነት በኢትዮጵያ አምራች ኢንዱስትሪ ከባቢ ውስጥ ምቹ የዲጂታላይዜሽን ምኅዳር ለመፍጠር በቁርጠኝነት እንደሚሰራ ተናግረዋል። የዲጂታላይዜሽን ሽግግር የኢንዱስትሪ ዕድገትን በማሳለጥ የምርት ጥራትና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን በማስጠበቅ የኢትዮጵያን የብልጽግና ጉዞ ለማሳለጥ የማይተካ ሚና እንዳለው አንስተዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የኢንዱስትሪ ዘርፍ ያስመዘገበውን እመርታዊ ዕድገት ለማስቀጠልም የዲጂታላይዜሽን መሰረተ ልማት ግንባታ ትኩረት እንደተሰጠው አብራርተዋል። በዲጂታል ሥርዓት የተመዘገቡ ውጤቶች በአምራች ኢንዱስትሪ ምርታማነት፣ የገበያ ትስስር፣ የመረጃ አያያዝና የምርት ጥራትን በማስጠበቅ ወሳኝ ድርሻ እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ቁልፍ ትልሞች የአምራች ኢንዱስትሪ የዲጂታል መሠረተ ልማትና የምርታማነት አቅም ለማሻሻል ገንቢ ሚና የሚጫወት መሆኑን ገልጸዋል። የአምራች ኢንዱስትሪ የገበያ አቅርቦት ትስስርና የግብዓት አቅርቦትን ለማሳለጥም ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው አንስተዋል።
የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረም በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Dec 29, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 20/2018 (ኢዜአ):- ዘጠነኛው የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረም የካቲት 9 እና 10 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን(ኢሴኤ) ከአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ሁነቱን ያዘጋጃል። ፎረሙ በአዲስ አበባ በየካቲት ወር ከሚካሄደው 39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ጎን ለጎን የሚደረግ ነው። “የአፍሪካን መጻኢ ጊዜ በፋይናንስ መደገፍ፤ ስራ እና ኢኖቬሽን ለዘላቂ ትራንስፎርሜሽን” የፎረሙ መሪ ሀሳብ ነው። የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረም በአፍሪካ የልማት እና የኢኮኖሚ እድገት ጉዳዮች ላይ ትኩረቱን በማድረግ በየዓመቱ የሚካሄድ ከፍተኛ አህጉራዊ የምክክር መድረክ መሆኑን ኢዜአ ከኢሲኤ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። አህጉራዊው መድረክ የአፍሪካ መሪዎች፣ ባለሀብቶች፣ የግሉ ዘርፍ ተዋንያንና የልማት አጋሮችን በአንድ መድረክ የሚያገናኝ ነው። ፎረሙ አጋርነትና የኢንቨስትመንት መጠንን ማሳደግ በተለይም የመንግስት እና የግል የተቀናጀ የፋይናንስ አቅርቦትን ጨምሮ የተለያዩ የፋይናንስ አማራጮችን ማስፋት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይት ይደረጋል። የስራ ዕድል፣ ምቹ የኢኖቬሽን ስነ ምህዳር እና የአፍሪካን የፈጠራ አቅም አሟጦ መጠቀም በፎረሙ ላይ ምክክር ከሚካሄድባቸው አጀንዳዎች ይጠቀሳሉ። በተለይም የዲጂታል ኢንዱስትሪዎች፣ የአነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች እንዲሁም እየሰፋ ያለውን የአፍሪካ የፈጠራ ዘርፍ ትኩረት ተሰጥቶባቸዋል። በፎረሙ የተለያዩ ኢኒሼቲቮች እና ማዕቀፎች ይተዋወቃሉ። የወጣቶችን የኢኖቬሽን ስራ ከፋይናንስ አቅርቦት ጋር የሚያስተሳስር የአፍሪካ የወጣቶች አይበገሬነትና ትራንስፎርሜሽን ማዕቀፍ ይፋ ይሆናል። በኢሲኤ የበለጸገውና የመንግስት እና የግሉ ዘርፍ የፋይናንስ ቃል ኪዳኖችን ትግበራ የሚከታታልና የሚቆጣጠር ስርዓትም በፎረሙ ይፋ ሆኖ ወደ ትግበራ ይገባል። ለሁለት ቀናት በሚቆየው ሁነት ላይ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች የምክክር መድረኮችና የባለሙያዎች ውይይቶች ይደረጋሉ። አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችና የፈጣራ ባለሙያዎችን ከባለሀብቶች እና ፋይናንስ አቅራቢዎች ጋር የሚያገናኝ አውደ ርዕይም ይካሄዳል። ሁነቶቹ ቃል ኪዳኖችን ወደ ተጨበጡ የኢኮኖሚ ፕሮጀክቶች ለመቀየር አስተዋጽኦ እንደሚያደርጉም ተመላክቷል። የአፍሪካ ቢዝነስ ፎረም በዘላቂ ልማት ግቦች እና በአጀንዳ 2063 የተቀመጡ ግቦች እንዲሳኩ ስትራቴጂካዊ ሚናውን እየተወጣ እንደሚገኝ መረጃው አመላክቷል።
ከኢኮኖሚ ስብራት ወደ ኢኮኖሚያዊ ማንሰራራት
Dec 29, 2025 88
አዲስ አበባ፤ ታኅሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም በተለያዩ ዘርፎች ተጨባጭ እና ዘላቂ የእድገት ውጤቶችን በማስመዝገብ ለጠንካራ እና ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ መሰረት መጣሉን የኢፌዴሪ መንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለጸ። የኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም በተለያዩ ዘርፎች ተጨባጭ እና ዘላቂ የእድገት ውጤቶችን በማስመዝገብ ለጠንካራ እና ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ መሰረት ጥሏል፡፡ የመንግሥት ቁርጠኝነት በታየበት በዚህ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ፕሮግራም ለዓመታት በኢኮኖሚው ላይ ተጋርጠው የነበሩ መዋቅራዊ ችግሮች ደረጃ በደረጃ እንዲቀንሱና ውስጣዊ ዐቅም ያለው፣ ከአለም ጋር የተሳሰረ እና በገበያ ተወዳዳሪ የሆነ ጠንካራ ኢኮኖሚ እንዲገነባ አስቻይ ዐውድ መፍጠር ተችሏል፡፡ የኢኮኖሚ እድገቱ በላቀ ደረጃ እንዲፋጠን በተለይ የዋጋ ግሽበትን በማረጋጋት፣ የውጭ ምንዛሬ ክምችቶችን በማሳደግ፣ ተኪ ምርቶችን በማበረታታትና፣ አዳዲስ የኢንቨስትመንት ፍሰቶችን በመሳብ ረገድ ማሻሻያው በእስካሁኑ ጉዞ ጉልህ ስኬቶችን አስመዝገቧል፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን መንግሥት በተከታታይ የወሰዳቸው ቁርጠኛ የማሻሻያ ውሳኔዎች ለተገኘው ስኬት መሰረቶች ናቸው፡፡ መንግሥት የኢኮኖሚ ስብራቱ እንዲጠገንና መልሶ እንዲያንሰራራ ከወሰዳቸው ቁልፍ እርምጃዎችና ካከናወናቸው አንኳር ስራዎች መካከል የውጭ የምንዛሬ ተመን በገበያ እንዲመራ እና የኢትዮጵያ ገንዘብ ትክክለኛውን ዋጋ እንዲያገኝ መደረጉ ነው፡፡ በዚህም ቀደም ሲል በህገ-ወጥ መንገድ ይዘዋወር የነበረው የውጭ ምንዛሬ ወደ ባንክ ህጋዊ ሥርዓት እንዲገባ በማድረግ በዶላር ዕጥረት ሊዘጉ ከጫፍ የደረሱ የኢንቨስትመንት ተቋማት ወደ ሥራ እንዲመለሱና ኢኮኖሚው ከገጠመው ከባድ ስብራት መልሶ እንዲያገግም ያስቻለ ውጤታማ ሥራ ማከናወን ተችሏል፡፡ ሌላው መንግሥት ካከናወናቸው ቁልፍ ተግባራት የሚጠቀሰው የውጭ ዕዳ ሽግሽግና ስረዛ እንዲደረግ የተሳካ ድርድር ማድረጉ ነው፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ ቀደም ሲል የወሰደቻቸው ብድሮች ከፍተኛ ወለድ የሚከፈልባቸው እና በአጭር ጊዜ የሚከፈሉ ኮሜርሻል ሎን በመሆናቸው ሀገርን ከባድ ፈተና ውስጥ ከተው ቆይተዋል፡፡ ይህን ችግር ለመቅረፍ መንግሥት ከአበዳሪ አገራትና ከፋይናንስ ተቋማት ጋር ባደረገው ስኬታማ ድርድር 4.5 ቢሊዮን ዶላር የሚጠጋ የዕዳ ሽግሽግ ማድረግ ተችሏል፡፡ በዚህም ሀገሪቱ ለውጭ ዕዳ መክፈያ ስትጠቀምበት የነበረው ሀብት፣ የሀገር ውስጥ የውጭ ምንዛሪ ክምችትን ለማሳደግና በመላ ሀገሪቱ እየተከናወኑ ላሉ የልማት ሥራዎች እንዲውል እድል ፈጥሯል፤ የፋይናንስ ተቋማትንም በእጅጉ አጠናክሯል፡፡ ከሁሉም በላይ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራው ያስገኘዉ ውጤት የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ፍሰት ግልጽና ሊተነበይ የሚችል የምንዛሬ ሥርዓት መፈጠሩ ነው፡፡ በዚህም የውጭ ባለሀብቶች በሀገራችን ላይ ያላቸው እምነት እንዲጎለብት፣ ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባው ካፒታል እንዲጨምር እና እንደሀገር ሁለተናዊ የኢኮኖሚ መነቃቃት እንዲፈጠር አድርጓል፡፡ በጥቅሉ የተደረገው የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሀገርን ከውድቀት በመታደግ፣ የውጭ ምንዛሬ ክምችትን በማሳደግ እና የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ጥንካሬ በማጎልበት ከአለም የንግድ ማኅበረሰብ ጋር ያላትን ግንኙነት ወደ ላቀ ምዕራፍ እንዲሸጋገር አድርጓል፡፡ የተገኙ ስኬቶች ዘላቂ እንዲሆኑ የወጪ ንግድን (Export) ማሳደግ፣ ተኪ ምርቶችንና ምርታማነትን መጨመር የመንግሥት ዋና ትኩረት ሆነው ይቀጥላሉ፡፡
በክልሉ የዋጋ ንረትን በዘላቂነት ለመከላከልና ሸማቹን ተጠቃሚ ለማድረግ በቅንጅት እየተሰራ ነው
Dec 29, 2025 68
ባሕርዳር፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ጥራትና ብዛት ያላቸው ምርቶችን ወደ ገበያ ማዕከላት በማስገባት የዋጋ ንረትን በዘላቂነት ለመከላከልና ሸማቹን ተጠቃሚ ለማድረግ ከአጋር አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑ ተገለጸ፡፡ በባሕርዳር ከተማ አስተዳደር አምራችና ሸማቹን በቀጥታ የሚያገናኝ የግብርናና ኢንዱስትሪ ምርቶች የቀረቡበት የገና ዋዜማ ባዛር ተከፍቷል። በባዛሩ ላይ 114 አቅራቢዎች፣ አምራቾች፣ ዩኒየኖችና ሕብረት ስራ ማህበራት ምርትና አገልግሎታቸውን ይዘው መቅረባቸው ተመልክቷል። የአማራ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢብራሂም መሃመድ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች አምራቹንና ሸማቹን በቀጥታ የሚያገናኙ የገበያ ማዕከላት ተገንብተው ለአገልግሎት በቅተዋል። በግንባታ ላይ የሚገኙ ማዕከላትንም በቅርቡ ለማጠናቀቅ እየተሰራ ነው ብለዋል። በቀጣይ ወደማዕከላቱ ጥራትና ብዛት ያላቸው ምርቶችን በማስገባት የዋጋ ንረትን በዘላቂነት ለመከላከልና ሸማቹን ተጠቃሚ ለማድረግ ከአጋር አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ከገበያ ማዕከላቱ በተጨማሪ የድንኳንና ሌሎች የገበያ አማራጮችን በማቅረብ ሸማቹ የሚፈልጋቸውን ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኝ የማድረጉ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በባሕርዳር የተከፈተውና ከዛሬ ጀምሮ ለዘጠኝ ተከታታይ ቀናት የሚቆየው የገና ዋዜማ ባዛር ላይ ለምግብነት የሚውሉ የተለያዩ የግብርናና ኢንዱስትሪ ምርቶች ለሸማቹ ማሕበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ እንደቀረቡም አስታውቀዋል። የክልሉ የግብርና ምርቶች መዳረሻ የገበያ ማዕከል ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ተዋቸው ወርቁ እንዳመለከቱት፤ የባዛሩ ዓላማ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ ማገናኘት ነው። ባዛሩ በማዕከሉ አስተባባሪነት ከክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ፣ ከባሕርዳር ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ፣ ከክልሉ ህብረት ስራ ኮሚሽንና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ እንደተዘጋጀም ገልጸዋል።
የሆሳዕና ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ለኑሮ ምቹ አድርጓል- ነዋሪዎች
Dec 29, 2025 57
ሆሳዕና፤ ታህሳስ 20/2018 (ኢዜአ) ፡-የሆሳዕና ከተማ የኮሪደር ልማትና የአስፓልት መንገድ ግንባታ ከተማዋን ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹና ተመራጭ ማድረጉን ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ነዋሪዎች መካከል አቶ ተመስገን ጌታሁን በከተማዋ እየተሰራ ያለው የመንገድና የኮሪደር ልማት ቀደም ሲል በየመንገዱ በሚጣል ደረቅና ፍሳሽ ቆሻሻን ለማስወገድ አስችሏል። በከተማዋ ኮሪደርን ጨምሮ የተከናወኑ የመሰረት ልማት ሥራዎች ንፁህ አካባቢን በመፍጠር ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ ማድረጉን ገልፀዋል፡፡ የከተማዋ ነዋሪ አቶ ደለለኝ ሻንቆ በበኩላቸው፤ የመንገዱ ግንባታ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴን በማሳለጥ የስራ እድል ፈጠራን እንዳሳደገው ጠቅሰዋል፡፡ የአስፓልት መንገዱ ግንባታ በአጭር ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት እንዲሆን የበኩላቸውን እንደሚወጡም ተናግረዋል፡፡ በከተማው የተገነቡት ዋና እና የውስጥ ለውስጥ መንገዶች በከተማዋ ፈጣን እድገት እንዲመዘገብ ጠቀሜታቸው የጎላ በመሆኑ ለልማቱ የአቅማቸውን ድጋፍ እንደሚያደርጉ የገለጹት ደግሞ የቦብቾ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አብርሃም ሻፊ ናቸው፡፡ መንገዶቹ የትራንስፖርት መጨናነቅን ከማስቀረት ባለፈ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እንዲፋጠን ማድረጋቸውን ተናግረዋል። የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሽጉጤ እንዳሉት፤ በከተማዋ በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር 15 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትር የዋና መንገድና ተለዋጭ የውስጥ ለውስጥ የአስፓልት መንገድ ግንባታ እየተከናወነ ነው፡፡ ከዚህ ውስጥ የ5 ኪሎ ሜትሩ የውስጥ ለውስጥ የአስፓልት መንገድ ግንባታ ሥራ ተጠናቋል ብለዋል። በተጨማሪም በከተማ አስተዳደሩና በህብረተሰቡ ተሳትፎ 12 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉን ነው የገለጹት። እነዚህ የአስፓልትና የኮሪደር ልማት ሥራዎች ከተማዋን ለነዋሪው ምቹና ፅዱ ከማድረግ ባለፈ ኢንቨስትመንትና ኮንፍረንስ ቱሪዝም እንዲስፋፉ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውንም አቶ ሳሙኤል አመልክተዋል።
በአማራ ክልል 266 ሺህ ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ዘር ተሸፍኗል
Dec 29, 2025 62
ደሴ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ከ266 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ዘር መሸፈኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በብልጽግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ይርጋ ሲሳይን ጨምሮ ሌሎች የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት በደዋ ጨፋ ወረዳ የበጋ መስኖ ስንዴና የፍራፍሬ ልማትን ጎብኝተዋል። የቢሮው ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ እንደገለጹት፣ በክልሉ የበጋ መስኖ ስንዴ ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት እየተሰራ ነው። ባለፉት ዓመታት በስንዴ ልማት ላይ በመጣው ውጤት አርሶ አደሩ ተጠቃሚነቱን እያረጋገጠ በመምጣቱ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማትን ባህል እያደረገው እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዚህም በዘንድሮው በጋ የመስኖ ስንዴ ልማት 350 ሺህ ሄክታር መሬት በማልማት 13 ነጥብ 6 ሚሊዮን ኩንታል ለማምረት ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን ተናግረዋል። እስካሁን በተደረገ እንቅስቃሴም ከ266 ሺህ ሄክታር መሬት በዘር መሸፈን መቻሉን ጠቁመው እቅዱን ለማሳካት በዘመቻ ጭምር የዘር ሥራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። ለዚህም በቂ ግብዓት በማቅረብ፣ የመካናይዜሽን ቴክኖሎጂዎችን ጥቅም ላይ በማዋልና አመራሩና ባለሙያው እስከ ታች ወርዶ ድጋፍና ክትትል እያደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል። አሁን ላይ አርሶ አደሩ ቡቃያውን ከአረምና ከተባይ በመከላከል ምርታማነቱን በማሳደግ የምግብ ዋስትናውን ማረጋገጥና ኢኮኖሚውን ማሳደግ ላይ አተኩሯል ነው ያሉት። በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን የደዋ ጨፋ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሃመድ ጌታቸው እንደገለጹት፣ በወረዳው የበጋ መስኖ ስንዴ ልማትን በማስፋት ምርታማነትን የማሳደግ ስራ በትኩረት እየተከናወነ ይገኛል። በዘንድሮው የበጋ ወቅትም ከ5 ሺህ 300 ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዶ እስካሁን ከ200 ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል ብለዋል። መንግስት በወቅቱ ያቀረበልንን ግብዓት ተጠቅመን በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት እየተሳተፍን እንገኛለን ያሉት ደግሞ በደዋ ጨፋ ወረዳ የሸክላ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መሀመድ እንድሪስ ናቸው። ግማሽ ሄክታር መሬታቸውን በዘር መሸፈናቸውን ጠቁመው ለሰብሉ ተገቢውን እንክብካቤ በማድረግ ከ20 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውን ተናግረዋል።
አርሶ አደሮች በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በሚያገኙት ገቢ ህይወታቸው እየተሻሻለ መጥቷል
Dec 29, 2025 70
ጭሮ ፤ ታህሳስ 20/2018(ኢዜአ)፦ በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በሚያገኙት ገቢ ህይወታቸው እየተሻሻለ መምጣቱን የምዕራብ ሐረርጌ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። በሀገር አቀፍ ደረጃ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከተጀመረ ወዲህ አርሶ አደሮች በልማቱ በንቃት በመሳተፍ ለራሳቸው እና ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ትልቅ አስተዋፅኦ እያበረከቱ ነው። የበጋ መስኖ ልማት ኢንሼቲቭ ቀደም ሲል ስንዴ አብቃይ ያልነበሩ አካባቢዎችን ወደ ልማቱ ከማስገባቱ በተጨማሪ የአርሶ አደሩን የስራ ባህል በመቀየርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ተጠቃሚ እያደረገ ይገኛል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የምዕራብ ሀረርጌ ዞን የቦኬ ወረዳ አርሶ አደሮች፤ የመስኖ ስንዴ ልማቱ በሀገር ደረጃ ከተጀመረ ወዲህ ወደ ልማቱ በመግባት በሚያገኙት ገቢ ህይወታቸው እየተሻሻለ መምጣቱን ገልጸዋል። በዞኑ በልማቱ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል ያህያ አደም፣ ዘንድሮ ሁለት ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ እያለሙ ይገኛሉ። የበጋ መስኖ ስንዴ ከመጀመሩ በፊት መሬቱ በጋ ላይ ከከብቶች መዋያነት ባለፈ ለልማት ውሎ አያውቅም ነበር ያሉት አርሶ አደሩ ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ ግን መሬቱን ወደ ልማት በማስገባት እስከ 50 ኩንታል ምርት እያገኙበት ነው። ባለፈው ዓመት ያመረቱትን ምርት ከራሳቸው አልፎ ለገበያ አቅርበው ከ300 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን አስታውሰዋል። ባገኙት ገቢም ፍየሎችንና በሬ በመግዛት ማድለብ መጀመራቸውን ጠቅሰው የበለጠ ተጠቃሚ ለመሆን እየተጉ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛው የቀበሌው አርሶ አደር አህመድ መሐመድ በበኩላቸው፤ ከሌሎች ስድስት አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በበጋ መስኖ ልማት እየተሳተፉ መሆናቸውን ተናግረዋል። ባለፈው ዓመት ያለሙትን የስንዴ ምርትም ከራሳቸው አልፎ ለገበያ ማቅረብ የቻሉ ሲሆን በዚህም ከ200 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ገልጸዋል። የቦኬ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ መሐመድዘይን ጀማል እንዳሉት፤ በዚህ ዓመት በወረዳው 10 ሺህ ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ እየለማ ነው። አርሶ አደሮቹ ዘመናዊ ቴክኖሎጂ እና ግብአት በመጠቀም በልማቱ ውጤታማ እንዲሆኑ በባለሙያ የቅርብ ድጋፍና እገዛ እየተደረገላቸው ነው ብለዋል። በዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት አስተባባሪ አቶ ሀቢብ አብዱልከሪም እንደገለጹት፤ በዞኑ ከ50 ሺህ በላይ አርሶአደሮችን በማሳተፍ ከ81 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የማልማት ስራ እየተከናወነ ይገኛል። እስካሁንም ከ26 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት በዘር መሸፈኑን በማንሳት በዞኑ ባለፉት ዓመታት እየተከናወነ ያለው የበጋ መስኖ ልማት ስራ ህዝቡን ከተረጂነት ለማላቀቅ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ 15 ወረዳዎች እየተከናወነ ባለው ልማትም ከሶስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱን አመልክተዋል። የምዕራብ ሀረርጌ ዞን የበጋ መስኖ ልማት ስራ ቀደም ብሎ ከሚጀምርባቸው የኦሮሚያ ክልል አካባቢዎች አንዱ ሲሆን የዘንድሮ በጋ መስኖ ልማት ስራም ከመስከረም መጨረሻ ጀምሮ ሲካሄድ መቆየቱ ተጠቅሷል።
የቻይና ገበያ ለኢትዮጵያ ቡና ያለው ፍላጎት እያደገ መምጣቱ ለኢትዮጵያ ትልቅ እድል ነው-አዱኛ ደበላ (ዶ/ር)
Dec 28, 2025 162
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ)፦ የቻይና ገበያ ለኢትዮጵያ ቡና ያለው ፍላጎት እያደገ መምጣቱ ለኢትዮጵያ ትልቅ እድል ነው ሲሉ የኢትዮጵያ ቡና እና ሻይ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር አዱኛ ደበላ ገለጹ። የኢትዮጵያን ቡናን በቻይና ገበያ የበለጠ ለማስተዋወቅ እና ኤክስፖርቱን ለማሳደግ ያለመ ኮንፍረንስ በቻይና ሁናን ግዛት እየተካሄደ ነው። ኮንፍረንሱ እያደገ የመጣውን የኢትዮጵያ እና ቻይና ጠንካራ ግንኙነት የሚያሳይ ሲሆን ወዳጅነታቸው በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂክ አጋርነት(all-weather strategic partnership) ምዕራፍ መሸጋገሩም ተገልጿል። ሁነቱ ኢትዮጵያን ጨምሮ የአፍሪካን ጥልቅ የኢኮኖሚ አቅም እንደሚያሳይ ተነግሯል። ቻይና የኢትዮጵያ ቡና ዋና መዳረሻ እየሆነች የመጣች ሲሆን የዛሬ አምስት አመት የኢትዮጵያን ቡና በመግዛት ከነበረችበት 33ኛ ደረጃ በተያዘው አመት ወደ 4ኛ ደረጃ ከፍ ብላለች። የቻይና ገበያ ለኢትዮጵያ ቡና ያለው ፍላጎት እያደገ መምጣቱ ለኢትዮጵያ ትልቅ እድል መሆኑን የኢትዮጵያ ቡና እና ሻይ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር አዱኛ ደበላ በወቅቱ ገልጸዋል። በቻይና የኢትዮጵያ አምባሳደር ተፈራ ደርበው በበኩላቸው፥ እያደገ የመጣውን የሁለቱን ሃገራት ግንኙነት በማንሳት ቡናም አንድ አስተሳሳሪ እየሆነ መምጣቱን አፅንኦት ሰጥተው ገልፀዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ኢፋ ሙለታ(ዶ/ር) በበኩላቸው፥ ኢትዮጵያ በግብርና መስክ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራትን በማንሳት በግብዓት፣ በውጤታማ የምርት አሰባሰብ፣ ክምችትና ሥርጭት መስኮች ተባብሮ ለመስራት ጥሪ አቅርበዋል። የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ተስፋሁን ጎበዛይ፣ቡና ለኢትዮጵያ ምርት ብቻ ሳይሆን ባህላዊ እሴትም መሆኑን በመግለፅ የሁለቱን ሃገራት የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚያግዝ አንስተዋል። ኮንፍረንሱ ቻይና በኢትዮጵያ ቡና ያላትን ተደራሽነት የበለጠ ለማሳደግና ወደ ቻይና የሚላከውን የቡና ኤክስፖርት መጠን ማሳደግ ያለመ መሆኑን ኢዜአ ከስፍራው ያገኘው ያመለክታል።
የሙያ ክህሎትን በመጠቀም በአነስተኛ ካፒታል የተጀመረ የስኬት መንገድ
Dec 28, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ)፦ የሙያ ክህሎትን በመጠቀም በአነስተኛ ካፒታል የተጀመረ የስኬት መንገድ የሥራ ቅጥር ከመፈለግ በርካታ ሰዎችን ወደ መቅጠር እንዳሸጋገራቸው በተለያየ የሙያ መስክ ሥራ ፈጣሪዎች ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ከልማት አጋሮች ጋር በመተባበር በአዲስ አበባ ወዳጅነት ፓርክ ያዘጋጀው የጥቃቅን፣ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ኤግዚቢሽንና ባዛር ተጠናቋል። ''ድምቅ በኢትዮጵያ ምርት" በሚል መሪ ሃሳብ ከታህሣስ 18 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ተከታታይ ቀናት በቆየው ባዛር ላይ የጥቃቅን፣ አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች ምርትና አገልግሎቶች ቀርበዋል። በኤግዚቢሽኑና ባዛሩ ላይ የተሳተፈው ኢምራን ሙህዲን፤በእንጨት የቅርፃ ቅርፅ ፈጠራ ሥራ ከእራሱ አልፎ ለሌሎችም የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጿል። በተሰማራበት አነስተኛ ሥራ የእንጨት ቅርፃ ቅርፅ የምርት ውጤቶችን በስፋት ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቱን እያሳደገ እንደሚገኝ ተናግሯል። በተመሳሳይ በኤግዚቢሽንና ባዛሩ ላይ የሹራብ ምርት ውጤቶችን ያቀረቡት ሃና መዴ፤ በአነስተኛ የገንዘብ መጠን የጀመሩት ሥራ ለሌሎች የሥራ ዕድል ያመቻቹበትን ውጤታማ አቅም መፍጠራቸውን ተናግረዋል። የፈጠሩት የሙያ ሽግግርም በአነስተኛ መነሻ ገንዘብ አቅም እየፈጠሩ እንደሚገኙ አንስተዋል። ጌጠኛ የክር ዘምቢል፣ ምንጣፍና ተያያዥ የፈጠራ ምርት ውጤቶችን ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታችን እያደገ ነው ያሉት ደግሞ በኤግዚቢሽንና ባዛሩ የተሳተፉት ቃል-ኪዳን ታደመ ናቸው። የማምረቻ ማሽኖችን ከውጭ በማስገባት አስራ አምስት እናቶችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ እያደረጉ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በኤግዚቢሽንና ባዛሩ የተሳተፉት ሌላኛዋ የፈጠራ ባለቤት ኤደን ኃይሉ፤ በአንድ ማሽንና በአነስተኛ ካፒታል በጀመርኩት የቆዳ ውጤቶች የማምረት ሥራ አሁን ላይ ከፍተኛ ዕድገት አስገኝቶልኛል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ከራሳቸው አልፎ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ማመቻቸታቸውን አንስተዋል።
በዞኑ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም በሰብል አሰባሰብ ወቅት የሚደርሰውን የምርት ብክነት ለመቀነስ ትኩረት ተደርጓል
Dec 28, 2025 177
ሮቤ፤ ታህሳስ 19/2018(ኢዜአ) :-በባሌ ዞን ዘመናዊ ቴክኖሎጂን በመጠቀም በሰብል አሰባሰብ ወቅት የሚደርሰውን የምርት ብክነት ለመቀነስ ትኩረት መደረጉን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሙአዊያ ፉአድ እንዳሉት በዞኑ በመኸሩ ወቅት በተለያዩ ሰብሎች የለማውን 538 ሺህ 500 ሄክታር መሬት በቴክኖሎጂ በመታገዝ ምርት የመሰብሰቡ ሂደት እየተከናወነ ነው። በቴክኖሎጂ የታገዘው የሰብል ስብሰባው ሂደት በድህረ ምርት ወቅት ሊያጋጥም የሚችለውን የምርት ብክነት ለመቀነስ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም ገልጸዋል። በዚህም የደረሰውን ሰብል ለመሰብሰብ በዞን ደረጃ ከ380 የሚበልጡ ኮምባይነሮች መሰማራታቸውን ለአብነት አንስተዋል። የመኸር አዝመራውን በመካናይዜሽን በመታገዝ ምርቱን የመሰብሰብ ስራው በዋናነት በዞኑ ሲናና እና ጋሠራ ወረዳዎች በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ እስከ አሁን በተደረገው ጥረት በመኸሩ ወቅት በዋና ዋና ሰብሎች ከለማው አጠቃላይ መሬት መካከል 65 ሺህ ሄክታር ላይ የለማው ሰብል ተሰብስቧል። ከተሰበሰበው ሰብል ከ2 ነጥብ 2 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መገኘቱን የጠቀሱት ምክትል ኃላፊው፤ ከአጠቃላይ ልማቱ ከ19 ነጥብ 1 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ አክለዋል። የደረሰን ሰብል ወቅቱን ካልጠበቀ ዝናብ ለመታደግ በኮምባይነር እየተደረገ ካለው የሰብል ስብሰባ በተጓዳኝ በአነስተኛ ማሽነሪዎችና በሰው ጉልበት የመሰብሰቡ ሥራም ተጠናክሮ መቀጠሉንም ነው የተናገሩት።
በበጋ መስኖ ልማት ከራሳችን አልፎ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ሆነናል-አርሶ አደሮች
Dec 28, 2025 132
ሀዋሳ፤ታህሳስ 19/2018 (ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል ሰሜናዊ ሲዳማ ዞን በበጋ መስኖ የጓሮ አትክልቶችን በማምረት ከራሳቸው አልፎ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ በበጋ መስኖ ከ35 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የጓሮ አትክልቶች እየለማ እንደሚገኝና 11 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ የዞኑ ገጠር ልማት መምሪያ አስታውቋል። በዞኑ ሀዋሳ ዙሪያ ወረዳ የጉድጓድ ውሀ በመጠቀም በመስኖ ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንዳሉት፥ በዓመት ሶስት ጊዜ የተለያዩ የጓሮ አትክልቶችን በማልማት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ሆነዋል። አርሶ አደር በርበራ ሌቲሞ በሀዋሳ ዙሪያ ወረዳ የጋሎ ኡርጌሳ ቀበሌ ነዋሪ ናቸው። አርሶ አደሩ ቀደም ባሉት ዓመታት የመስኖ ልማት ስራዎች ላይ ተሳትፈው አያውቁም። የበልግና የክረምት ዝናብን ጠብቀው ያለሙት የነበረው በቆሎ ከቤት ውስጥ ፍጆታ ያለፈ ጥቅም ሳያስገኝላቸው እሳቸውም ሳይለወጡ ዘመናትን ተሻግረዋል። ካለፈው ዓመት ጀምሮ በመስኖ ልማት በመሳተፍ ባላቸው አንድ ሄክታር መሬት ላይ ጥቅል ጎመን፣ ቃሪያና ቲማቲም እያለሙ ይገኛሉ። በሶስት ዙር ባለሙት የአትክልት ምርትም ተጠቃሚ መሆን እንደቻሉና አምና ከጥቅል ጎመን ሽያጭ ብቻ 310 ሺህ ብር ማግኘት እንደቻሉ ይናገራሉ። አሁን እያመረቷቸው ከሚገኙት የአትክልት ምርቶችም ከዚሀ ቀደሙ ከሚያገኙት የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁም አርሶአደሩ ገልጸዋል። አርሶ አደር አጌርሶ ደበላ ደግሞ ከቀደሙት አርሶ አደር በተለየ ሁኔታ በመስኖ ስራ መሳተፍ ከጀመሩ አራት ዓመት ሆኗቸዋል። ከመስኖ ልማት የሚገኘውን ጥቅም ቀደም ብለው የተረዱ አርሶ አደር ነበሩና ከሌላ ጎረቤታቸው ጋር በመሆን 22 ሄክታር መሬት በቃሪያ፣በጥቅል ጎመንና በቲማቲም ማልማታቸውን ይገልጻሉ። ''ከልማቱ የሚገኘውን ጥቅም ያወቀ አርሶ አደር መተኛት የለበትም'' የሚሉት አርሶ አደሩ በሄክታር እስከ 12 የጭነት አይሱዙ ሙሉ የቲማቲም ምርት እንደሚያገኙ ጠቁመዋል። አምና ካለሙት ቲማቲምና ጥቅል ጎመን 7 ሚሊዮን ብር እንዳገኙ የተናገሩት አርሶ አደሩ በዘንድሮ ዓመትም በእጥፍ ተጠቃሚ ለመሆን እንደሚጠብቁም ይናገራሉ። የሀዋሳ ዙሪያ ወረዳ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዲሱ ደሳለኝ እንዳሉት፥ በወረዳው አርሶ አደሩን በክላስተር በማደራጀት በበጋ መስኖ ስራ እንዲሳተፍ እየተደረገ ይገኛል። በሀዋሳ ዙሪያ ወረዳ 174 የመስኖ ክላስተሮች እንዳሉ ገልጸው፥ አርሶ አደሮቹ ተመሳሳይ ምርት አምርተው ገበያ እንዳያጡ ቲማቲም፣ ጥቅል ጎመን፣ ቃሪያ፣ ሽንኩርትና ሌሎች የጓሮ አትክልቶችን በማሰባጠር እንዲያለሙ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በተያዘው የበጋ ወቅትም ዘጠኝ ሺህ 720 ሄክታር መሬት በማልማት 3 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ወደ ስራ እንደተገባና በዚህም ከ14 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። የዞኑ ገጠር ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ ዱሬሳ ሌዳሞ እንዳሉት፥ የውሀ አማራጭ ባለባቸው አካባቢዎች የወንዝና የጉድጓድ ውሀን በመጠቀም 35 ሺህ 254 ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ እየለማ ይገኛል። የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና በማረጋገጥ ከተረጂነት ለማውጣት የተያዘውን ግብ ለማሳካት በዞኑ ከ700 ሄክታር በላይ መሬት ማልማት የሚያስችሉ አምስት ጥልቅ ጉድጓዶችን በማዘጋጀት የመስኖ ልማት ስራው በትኩረት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪም አርሶ አደሩ በግሉ አነስተኛ የውሀ ጉድጓድ እንዲያዘጋጅ በማድረግ 3 ሺህ 700 የውሀ መሳቢያ ሞተር በማሰራጨት ከ35 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት እየለማ እንደሚገኝም ተናግረዋል። እየለማ ከሚገኘው መሬትም 11 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል።
የመኸር ምርት ወደ ገበያ እየገባ መሆኑን ተከትሎ የምግብ እህል የዋጋ ቅናሽ አሳይቷል - የወልዲያ ከተማ ነዋሪዎች
Dec 28, 2025 69
ወልዲያ፤ታህሳስ 19/2018( ኢዜአ)፡- በአሁኑ ወቅት የመኸር ምርት ወደ ገበያ እየገባ መሆኑን ተከትሎ የምግብ እህል የዋጋ ቅናሽ ማሳየቱን ኢዜአ ያነጋገራቸው የወልዲያ ከተማ ነዋሪዎች። በአብዛኛው የአገሪቱ አካባቢዎች የመኸር ምርት አሰባሰብ ሂደት እየተገባደደ ሲሆን ቀደም ብሎ የተሰበሰበው የሰብል ምርትም ለገበያ እየቀረበ ነው። ኢዜአ ካነጋገራቸው የወልዲያ ከተማ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ብዙነሽ ዓለሙ፣ የዘንድሮው የመኸር ምርት ተሰብስቦ ለገበያ መቅረብ በመጀመሩ የእህል ገበያው ቅናሽ እያሳየ ነው ብለዋል። በዚህም 12 ሺህ ብር ይሸጥ የነበረው የአንድ ኩንታል ነጭ ጤፍ አሁን ላይ 10 ሺህ 500 እየተሸጠ መሆኑን ጠቅሰው ሰርገኛ ጤፍ ደግሞ ከ11 ሺህ ወደ 9 ሺህ 500 መቀነሱን ገልጸዋል። የግብርና ምርትን ከአርሶ አደሩ በቀጥታ የሚገዙበት ሁኔታ በመመቻቸቱም ይበልጥ ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን ተናግረዋል። ሌላዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ አስማረች ምስጋናው፤ የመኸር ምርት ከመሰብሰቡ በፊት 8 ሺህ 500 ብር ይሸጥ የነበረው አንድ ኩንታል ማሽላ አሁን ላይ 7 ሺህ ብር መግዛታቸውን አንስተዋል። በአሁኑ ወቅት ግብይቱ በአብዛኛው ቀጥታ ከአርሶ አደሩ መሆኑን ገልጸው ይህም ህገወጥ ነጋዴዎችና ደላሎችን ለመከላከል ማገዙን ተናግረዋል። የወልዲያ ከተማ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ አዲሱ ወንድሙ በበኩላቸው በመኸር አዝመራ የለማ ሰብል ተሰብስቦ ለገበያ እየቀረበ በመሆኑ የዋጋ መረጋጋት ታይቷል ብለዋል። ምርቱ ሙሉ በሙሉ ተሰብስቦ ሲጠናቀቅ ገበያው ከአሁኑ በተሻለ እንደሚረጋጋ ይጠበቃል ያሉት ኃላፊው በአርሶ አደሩ እየቀረበ ያለው ምርት በቀጥታ ለሸማቹ የሚደርስበት ምቹ ሁኔታም ተፈጥሯል ብለዋል። የወልዲያ ከተማ ህብረት ሰራ ማህበራት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አንተነህ ሲሳይ፣ የከተማው ህብረት ስራ ማህበራት የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የሚያስችል የጤፍ ግዥ እያከናወኑ ነው ብለዋል። እስካሁንም ከተለያዩ አካባቢዎች ጤፍ እየገዙ መሆኑን ጠቁመው ምርቱ በተመጣጠኝ ዋጋ ለሸማች እንደሚቀርብም ገልጸዋል። በተጨማሪም ማህበራቱ ፓስታ፣ ማካሮኒ፣ ዱቄትና ሌሎች የኢንዱስትሪ ውጤቶችን በመግዛት ለሸማቹ እያቀረቡ እንደሚገኙም አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለሕንድ ባለሃብቶች ምቹ የኢንቨስትመንት ምኅዳር ፈጥሯል
Dec 28, 2025 94
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለሕንድ ባለሃብቶች ምቹ የኢንቨስትመንት ምኅዳር መፍጠሩን በኢትዮጵያ የሕንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ገለጹ። ኢትዮጵያ ለሕንድ አልሚ ባለሃብቶች ምቹ የልማት ከባቢ የፈጠረች ሀገር መሆኗንም በተለያዩ የኢንቨስትመንት አማራጮች የተሰማሩ ሕንድ ባለሃብቶች ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የሕንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ ከፍተኛ ኢንቨስትመንት ካላቸው ሀገራት መካከል ሕንድ ከግንባር ቀደምቶቹ አንዷ ናት። በዚህም የሕንድ ባለሃብቶች ኢትዮጵያ ትኩረት በሰጠቻቸው የጤና፣ የግብርና፣ ጨርቃ ጨርቅና ሌሎች መስኮች አምስት ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር የሚደርስ ኢንቨስትመንት እንዳላቸው ተናግረዋል። በቀጣይም የሕንድ ባለሃብቶች የኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት ዕድል በመጠቀም በሥራ ዕድል ፈጠራና ምርታማነት ላይ በስፋት እንዲሳተፉ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ አንስተዋል። የሕንድ አልሚ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ ያላቸው የኢንቨስትመንት ልማት ለበርካታ ኢትዮጵያውያን በሥራ ዕድል ፈጠራና በዲጂታላይዜሽን የቴክኖሎጂ ሽግግር ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ ተግባራዊ የሆነው ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር ለሕንድ ባለሃብቶች የኢንቨስትመንት ፍሰት ምቹ ምኅዳር መፍጠሩን አብራርተዋል። በኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ከተሰማሩ የሕንድ አልሚዎች መካከል የሞሀን ግሩፕ ድርጅቶች ሥራ አስኪያጅ ሀርሽ ኮታሪ፤ የኢትዮ-ሕንድ የዳበረ ግንኙነት የኢንቨስትመንት አድማሳችን ለማስፋት ዕድል ፈጥሮልናል ብለዋል። የኢትዮጵያና ሕንድ ታሪካዊ ወዳጅነት ወደ ስትራቴጂክ አጋርነት መሸጋገሩም የሕንድ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ የሚኖራቸውን ዘርፈ ብዙ ኢንቨስትመንት ለማሳደግ ወሳኝ ዕድል እንደሚፈጥር ገልጸዋል። የካዲላ ፋርማሲዩቲካል ኢትዮጵያ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ሬጂ ጆን፤ የሕንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሪንድራ ሞዲ የኢትዮጵያ ጉብኝት የሀገራቱን ስትራቴጂክ አጋርነት ለማጎልበት ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝትና የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚክ ማሻሻያም የሀገራቱን የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር በማሳደግ የሕንድ ባለሃብቶችን የኢንቨስትመንት ፍሰት እንደሚያሳድግ ገልጸዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድቡ ጥበብ የተሞላበት አመራር ውጤት ነው
Dec 27, 2025 113
አዲስ አበባ፤ ታኅሳስ 18 /2018(ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድቡ ጥበብ የተሞላበት አመራር ውጤት መሆኑን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ርስቱ ይርዳው ገለጹ። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከፍተኛ አመራሮች ታላቁ የኢትዮጵ ህዳሴ ግድብን በዛሬው ዕለት ጎብኝተዋል። የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ርስቱ ይርዳው በዚሁ ወቅት የህዳሴ ግድብ እውን የሆነው ጥበብ የተሞላበት አመራር በመሰጠቱ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ እንደ ሀገር በርካታ ፈተናዎችን በመቋቋም ዳግማዊ አድዋ የሆነውን የህዳሴ ግድብ በማጠናቀቅ ያስመዘገበችው ድል የሚደነቅ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የግድቡ ግንባታ ተጠናቆ ወደ ተግባር ምዕራፍ መሸጋገሩ የላቀ ሀገራዊ ፋይዳ ያለው መሆኑንም አመልክተዋል። ምንም እንኳ አንዳንድ አካላት አሁንም የግድቡን ፋይዳ በግልፅ ባለመረዳት የተለያዩ ፕሮፖጋንዳዎችን እያሰራጩ ቢሆንም፤ ኢትዮጵያ ግን እራሷን ከድህነት ለማላቀቅ እና ዜጎቿ የተሻለ የኑሮ ዘይቤ እንዲኖራቸው በማለም ያላትን እምቅና ተፈጥሮአዊ ሀብት የመጠቀም መብትን መሰረት በማድረግ እንዲሁም ፈተናዎችን ድል በመንሳት ግድቡን እውን ማድረግ ችላለች ብለዋል። አቶ ርስቱ የህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያዊያን ሁሉ አሻራ ያረፈበት መሆኑን በመግለፅ፤ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አመራሮችና ሠራተኞችም በተለያየ ደረጃ የሚገለጽ ጉልህ ሚና ማበርከታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ አሁንም አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ከተሰጠው ሀገራዊ ተልዕኮ በመነጨ ለግድቡ ደኅንነት የሚያደርገውን ክትትል እና ጥበቃ አጠናክሮ የቀጠለ መሆኑን አመልክተዋል፡፡ በጉብኝቱ ተሳታፊ የነበሩ የአገልግሎቱ ከፍተኛ አመራሮች የህዳሴ ግድብን በቦታው ተገኝቶ መመልከት ልዩ ስሜትን ይፈጥራል ሲሉ ተናግረዋል። ታላቁን የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለመገንባት ብዙ ተደክሞበታል የኢትዮጵያ ሕዝብም ጥሪት ነው ያሉት የተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች፤ በቀጣይም ግድቡ ያለምንም የፀጥታ ስጋት አገልግሎት እንዲሰጥ ማድረግ እና የሀገሪቱን ሰላምና ደኅንነት ማስጠበቅ የተቋሙ ዋነኛ ተልዕኮ መሆኑን ገልፀዋል። አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ከሌሎች አቻ ተቋማት ጋር በመቀናጀት በመረጃ እና በደኅንነት ስምሪት ቀጣይነት ያላቸው ስራዎች እንደሚሰራም ከፍተኛ አመራሮቹ መግለጻቸውን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ የላከው መረጃ አመልክቷል።
የኢትዮጵያ እና ቻይና አጋርነት በተገነባበት ጠንካራ መሰረት ጸንቶ ይቀጥላል - ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ
Dec 27, 2025 152
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 18/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ እና ቻይና የረጅም ጊዜ አጋርነት በጠንካራ መሰረቱ ጸንቶ ይቀጥላል ሲሉ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ገለጹ። የኢትዮጵያ ቡናን በቻይና ገበያ የበለጠ ለማስተዋወቅ እና ኤክስፖርቱን ለማሳደግ ያለመ ኮንፍረንስ በቻይና ሁናን ግዛት እየተካሄደ ነው። ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ኮንፍረንሱን በማስመልከት መልዕክት አስተላልፈዋል። ፕሬዝዳንት ታዬ የኢትዮጵያ እና ቻይና አጋርነት ለረጅም ጊዜ ፀንቶ የቆየ ግንኙነት እንዳላቸው ገልጸዋል። የቡና መገኛ የሆነችው ኢትዮጵያ ለዓለም በርካታ ባለልዩ ጣዕም ቡና ምርቶችን እያቀረበች እንደምትገኝ አመልክተዋል። ቡና ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንት ነው ያሉት ፕሬዝዳንቱ በስራ እድል ፈጠራ 25 በመቶ እና በውጭ ምንዛሬ 30 በመቶ ድርሻ እንዳለውም ጠቁመዋል። ኮንፍረንሱ እያደገ የመጣውን የኢትዮጵያ እና ቻይና ጠንካራ ግንኙነት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸው ወዳጅነታቸው በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂክ አጋርነት(all-weather strategic partnership) ምዕራፍ መሸጋገሩንም ነው ያወሱት። ሁነቱ ኢትዮጵያን ጨምሮ የአፍሪካን ጥልቅ የኢኮኖሚ አቅም እንደሚያሳይ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ እና ቻይና ግንኙነት በቻይና-አፍሪካ ትብብር ፎረም(ፎካክ) አማካኝነት በግብርና፣ የገጠር አረንጓዴ ልማት ንግድና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ትስስር የኢንዱስትሪ ትራንስፎርሜሽንን ለማምጣት እየተሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል። የአፍሪካ እና ቻይናን የንግድ ትብብር ዘላቂ እና ባለብዝሃ ዘርፍ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችንም አንስተዋል። በቻይና ሁናን ግዛት ጁጆ ከተማ የኢትዮጵያ የቡና ስርጭት ማዕከል መከፈቱ ኢትዮጵያ በሰፊው የቻይና የቡና ገበያ ያላት ድርሻ እንዲያድግ የበኩሉን ሚና ይወጣል ነው ያሉት ፕሬዝዳንቱ። ከኢትዮጵያ የልማት ግቦች ጋር የተጣጣሙ የቻይና የኢንዱስትሪ ልማት ኢኒሼቲቮች በሌሎችም መስኮች ሊሰፋ እንደሚገባ ጠቁመው ይህም ኢትዮጵያን ጨምሮ የአፍሪካ ሀገራት በዓለም እሴት ሰንሰለት ውስጥ ድርሻቸው እንዲያድግ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት አብራርተዋል። ፕሬዝዳንት ታዬ ኮንፍረንሱ ስኬታማ እንዲሆን አስተዋጽኦ ያበረከቱ አካላትም አመስግነዋል። በቻይና ሁናን ግዛት ጁጆ ከተማ በተዘጋጀው ኮንፍረንስ ከ700ሺህ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የኢትዮጵያን ባለልዩ ጣዕም ቡና ለማስቀመስ እቅድ ተይዟል። ቻይና የኢትዮጵያ ቡና ዋና መዳረሻ እየሆነች የመጣች ሲሆን የዛሬ አምስት አመት የኢትዮጵያን ቡና በመግዛት ከነበረችበት 33ኛ ደረጃ በተያዘው አመት ወደ 4ኛ ደረጃ ከፍ ብላለች። ኮንፍረንሱ ቻይና በኢትዮጵያ ቡና ያላትን ተደራሽነት የበለጠ ለማሳደግና ወደ ቻይና የሚላከውን የቡና ኤክስፖርት መጠን ማሳደግ ያለመ መሆኑን ኢዜአ ከስፍራው ያገኘው ያመለክታል።
በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በእንስሳት ዘርፍ የተገኘው ስኬት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Dec 27, 2025 84
ሀዋሳ፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡- እንደ ሀገር በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የእንስሳት ዘርፍ ላይ የተገኘውን ስኬት አጠናክሮ ለማስቀጠል ለእንስሳት አያያዝና ጤና ትኩረት መሰጠቱን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። በግብርና ሚኒስቴር እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት ዘርፍ የዶሮ ፣ የወተት ላሞችና የጥጆች አያያዝ እና ጤና አጠባበቅ ላይ ያተኮረ የአሰልጣኞች ሥልጠና ለዘርፉ አመራርና ባለሙያዎች በሀዋሳ ከተማ እየተሰጠ ነው፡፡ በሥልጠናው መድረክ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር)፤ የሌማት ትሩፋት መርሀ ግብር በኢትዮጵያ የእንስሳት ቁጥርን መሠረት ካደረገ የተለመደ አሰራር በመውጣት ዘመናዊውን በመከተል ምርታማነትን ይበልጥ ማሳደግ እንዳስቻለ ተናግረዋል። ከዚህ አኳያ በዝርያ ማሻሻል ፣ በግብአት አቅርቦት ፣ በምርትና ሌሎች ሥራዎች በአጭር ጊዜ ውስጥ ትላልቅ እመርታዎች መምጣታቸውን አስረድተዋል፡፡ እንቁላል ፣ ወተትና ሌሎች የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች ከቤተሰብ ፍጆታ ባለፈ በስፋት ወደ ገበያ የሚቀርብበትና የዜጎችንም ገቢ ማሻሻሉን አንስተዋል፡፡ የወተት ምርት በክልሎች ከአካባቢ ገበያ አልፎ ለአዲስ አበባ እንዲሁም ለማቀነባበሪያ ፋብሪካዎች በስፋት እየቀረበ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል፡፡ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸውን እንስሳት እና የመኖ አቅርቦትና እንክብካቤ በማድረግ እንዲሁም ጤናቸውን በመጠበቅ ምርታማነትን ለማላቅ ከፍተኛ ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል፡፡ በሚኒስቴሩ የእንስሳት ጤና ፣ በሽታ መከላከልና ቁጥጥር ዴስክ ኃላፊ ሜሮን ሞገስ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ እንደ ሀገር የእንስሳት በሽታን መከላከል መሠረት ያደረገ የጤና አጠባበቅ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል፡፡ በሽታዎች ሲከሰቱ አፋጣኝ ምላሽ መስጠት እንዲያስችልም በየአካባቢው የእንስሳት ክሊኒኮች እንዲስፋፉ አቅጣጫ ተቀምጦ እየተተገበረ እንደሚገኝ ጠቁመዋል ፡፡ በእንስሳት አያያዝና ጤና አጠባበቅ ላይ የተደራጀ መረጃ የያዙ መመሪያ ዶክመንቶች ለማስተግበር የሚያስችል ሥልጠና እየተሰጠ እንደሚገኝም አውስተዋል፡፡ በክልሉ እያደገ ባለው የተሻሻሉ የእንስሳት ዝርያዎች ቁጥር ልክ የክትባትና ሌሎች የጤና አጠባበቅ ሥራዎች መሻሻላቸውን የገለጹት ደግሞ የሲዳማ ክልል እንስሳት ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሰፋ ፎና ናቸው። በየቀበሌው አንድ የእንስሳት ጤና ኬላ እንዲሁም በሁሉም ወረዳዎች የእንስሳት ጤና ክሊኒኮችን የመገንባት ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በሥልጠናው ላይ ከሲዳማ ፣ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ፣ ደቡብ ኢትዮጵያና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልሎች የተውጣጡ የዘርፉ አመራርና ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ፡፡
የጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርቶችን በስፋት እንዲያቀርቡ በግብአትና ምርምር እየታገዙ ነው
Dec 27, 2025 112
ባሕር ዳር ፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡-የጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪዎች ተኪ ምርቶችን በስፋት ማቅረብ እንዲችሉ በበቂ ግብዓትና ምርምር እየታገዙ መሆኑ ተገለጸ። በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ የቴክስታይልና ፋሽን ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት በዘርፉ ላይ ያተኮረ አውደ ጥናት ዛሬ አካሄዷል። በአውደ ጥናቱ የተገኙት በግብርና ሚኒስቴር የጥጥ ልማት መሪ ስራ አስፈፃሚ ሳምሶን አሰፋ እንደተናገሩት፤ ለሃገር ውስጥ የጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪዎች ጥራቱን የጠበቀ በቂ የጥጥ ምርት እየቀረበ ነው። በዚህም ባለሃብቶችን በዘርፉ የማሰማራትና የአርሶ አደሮችን ምርታማነት በማሳደግ የጥጥ ምርት ጥራትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት በትብብር እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም በምርምር ከማገዝ ባለፈ ምርጥ ዘር የማቅረብና ሌሎች ግብዓቶችን የማሟላት ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በጥጥ የሚለማው መሬት ባለፉት አምስት ዓመታት እያደገ መምጣቱን አንስተው፤ ባለፈው የመኽር ወቅትም 110 ሺህ ሄክታር መሬት በጥጥ መልማቱን አብራርተዋል። ለዘርፉ ኢንዱስትሪዎች በቂ ጥጥ ከማቅረብ ባሻገር ባለፈው ዓመት ከፍጆታ የተረፈውን ምርት ለውጭ ገበያ ማቅረብ እንደተቻለም አውስተዋል። የተገኘውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠልም ዘርፉን በምርምር ለማገዝ ኢንዱስትሪዎችን፣ ዩኒቨርስቲዎችና ሌሎች ባለድርሻ ተቋማትን ያካተተ ብሄራዊ ፎረም ተዋቅሮ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ የቴክስታይልና ፋሽን ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ታምራት ተስፋዬ በበኩላቸው፤ የቴክስታይል ዘርፍ ለኢኮኖሚ እድገቱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑን ተናግረዋል። ዘርፉን ለማዘመን በበቂ መጠን የሰለጠነ የሰው ሃይል ከማፍራት ባለፈ ለጥናትና ምርምር ስራዎች ሰፊ እገዛ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። በሃገሪቱ ከሚገኙ 114 ኢንዱስትሪዎች ጋር ትስስር በመፍጠር በምርት ብዛትና ጥራት ተፎካካሪ እንዲሆኑ እገዛ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። ተኪ ምርትን በሃገር ውስጥ ማምረት መንግስት ትኩረት ከሰጣቸው ዘርፎች አንዱ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለዚህም ላቦራቶሪዎችን በማደረጀት፣ የራሱን ፋብሪካ በማቋቋም፣ ተማሪዎችን በማስተማርና የምርምር ስራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛል ብለዋል። የዛሬው አውደ ጥናትም ቅንጅታዊ አሰራርን አጠናክሮ ለማስቀጠል ያለመ መሆኑን አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ዋና ስራ አስፈፃሚ ፕሮፌሰር ተከተል ዮሐንስ፤ የቴክስታይል ዘርፉን ለማዘመን ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት፣ የግብርናው ዘርፍና ኢንዱስትሪዎች በትስስር መስራት እንዳለባቸው ተናግረዋል። ለኢንዱስትሪዎች የሚቀርበው የጥጥ ምርት ጥራቱን የጠበቀ መሆን እንዳለበት አንስተው፤ ለዚህም በምርምር የታገዘ ስራን ማጠናከር ተገቢ እንደሆነም አንስተዋል። በአውደ ጥናቱ ከፌደራል ተቋማት፣ ከኢንስቲትዩቱና ከሌሎች ዩኒቨርስቲዎች የተወጣጡ የዘርፉ ምሁራንና ተማሪዎች ተሳትፈዋል።
በክልሉ ከ78 ሺህ በላይ የቤተሰብ መሪዎች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ተሸጋግረዋል
Dec 27, 2025 65
ዲላ፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በ5ኛ ዙር ልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም በተደረገላቸው ድጋፍ ከ78 ሺህ በላይ የቤተሰብ መሪዎች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት መሸጋገራቸውን የክልሉ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ገለጸ። በጌዴኦ ዞን በአምስተኛ ዙር ልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የተሸጋገሩ 6ሺህ 111 የቤተሰብ አስተዳዳሪዎች ዛሬ በዲላ ከተማ ተመርቀዋል። የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር ሽፈራው ቦጋለ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ በክልሉ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር በልማታዊ ሴፍቲኔት ለታቀፉ የቤተሰብ አስተዳዳሪዎች የተለያዩ ድጋፎች እየተደረገ ነው። በአምስተኛ ዙር የልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም በተደረገላቸው ድጋፍ ከ78 ሺህ በላይ የቤተሰብ አስተዳዳሪዎች ከተረጂነት ተላቀው ራሳቸውን በመቻል ወደ ምርታማነት መሸጋገራቸውን ገልጸዋል። ዛሬ የተመረቁ የቤተሰብ መሪዎችም ትጋታቸውን በመቀጠል ከራሳቸው ባለፈ ለሌሎች መትረፍ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። በዞኑ የልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራም ተግባራዊ ከተደረገ ጊዜ አንስቶ በርካቶችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ያነሱት ደግሞ የጌዴኦ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ተገኝ ታደሰ ናቸው። ይህም በምግብ ራስን ለመቻል የሚደረገውን ጥረት ከማገዝ ባለፈ ዜጎች ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ተሸጋግረው ተጠቃሚ እንዲሆኑ አስችሏል ብለዋል። የዛሬ ተመራቂዎችም በፕሮግራሙ ድጋፍ ያገኙትን ክህሎትና ያካበቱትን ሃብት አቀናጅተው ለበለጠ ውጤት መትጋት እንዳለባቸው አስረድተዋል። የጌዴኦ ዞን አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ዶክተር ተድላ ጌታሁን በበኩላቸው፤ ዛሬ ከተረጂነት ተላቀው የተመረቁ 6 ሺህ 111 የቤተሰብ አስተዳዳሪዎች በዞኑ አራት ወረዳዎች ባለፉት ሦስት ዓመታት የልማታዊ ሴፍትኔት ፕሮግራም ተጠቃሚ እንደነበሩ አስታውሰዋል። በተለይ በሌማት ትርፋት፣ በአረንጓዴ ልማት፣ በእንስሳት እርባታና ሌሎች ዘርፎች ተሰማርተው ውጤታማ መሆናቸው መረጋገጡን አንስተዋል። በዚህም በርካቶች ለራሳቸው ቋሚ ገቢና ሥራ ከመፍጠር ባለፈ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትና ችግራቸውን መፍታት እንደቻሉ አስረድተዋል። ከተጠቃሚዎች መካከል የወናጎ ወረዳ ነዋሪ አቶ ማቲዎስ ሌጌ፤ በተደረገላቸው ድጋፍ ኑሯቸውን መቀየሩን አንስተዋል። በንብ ማነብና በእንስሳት እርባታ ዘርፎች መሰማራታቸውን ጠቅሰው በተለይ ለገበያ ከሚያቀርቡት የማር ምርት ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም ተቀማጭ ካፒታላቸው ከ200 ሺህ በላይ መድረሱን አንስተው ለተደረገላቸው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።
በክልሉ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል
Dec 27, 2025 154
ወላይታ ሶዶ፤ ታኅሣስ 18/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አምራቹንና ሸማቹን በማገናኘት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገለጸ። የክልሉ ሕብረት ሥራ ልማት ኤጀንሲ ከክልሉ አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የሕብረት ሥራ ማህበራት የንቅናቄ መድረክ በወላይታ ሶዶ ከተማ ተካሂዷል። "ጠንካራ የቁጠባና ሕብረት ሥራ ማህበራት ለምግብ ዋስትና እና ለሥራ ዕድል ፈጠራ" በሚል መሪ ሃሳብ በተካሄደው የንቅናቄ መድረክ ላይ የክልሉ የመንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ ንጋቱ ዳንሳ ፤ በክልሉ ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ እየቀረቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይ የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በስፋት በማቅረብ አምራቹና ሸማቹን በማገናኘት ገበያን ለማረጋጋት በሚሰራው ሥራ የሕብረት ሥራ ማህበራት ድርሻ የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የሕብረት ሥራ ማህበራትን አቅም በማጎልበት በኢኮኖሚው ዘርፍ ያላቸውን አስተዋጽኦ ለማሳደግና ህገ ወጥ ደላሎችን ከገበያ ለማስወጣት በቅንጅት መስራት ይገባል ብለዋል። በየአካባቢው አምራቹንና ሸማቹን በማገናኘት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ የተጀመረው ሥራ ውጤት እያስገኝ በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም ገልጸዋል። ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም መተግበሩን ተከትሎ ሕብረት ሥራ ማህበራት ተወዳዳሪና ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቁመው፣ ሁሉም ዜጋ በነፃ ገበያ የኢኮኖሚ ስርዓት ውስጥ እንዲወዳደር መስራት ይገባል ብለዋል። ከሀገራዊ ለውጥ ወዲህ የኅብረት ሥራ ማህበራት ያሉባቸውን ተግዳሮቶች በመፍታት በኢኮኖሚና ማህበራዊ ዕድገት ላይ የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲወጡ የአሰራር ሥርአት መዘርጋቱን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ህብረት ሥራ ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳሙኤል ፎላ ናቸው። በክልሉ 2 ነጥብ 57 ቢሊዮን ካፒታል ያፈሩ 6 ሺህ 381 መሰረታዊና 30 የህብረት ሥራ ዩኒዬኖች እንዳሉ ጠቁመው በእነዚህም 1 ሚሊዮን 178 ሺህ በላይ አባላት ታቅፈው ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። ማህበራቱ ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ ብድር በማሰራጨትና የፋይናንስ ትስስር በመፍጠር አባላቱ በገቢ ማስገኛ ዘርፎች ተሰማርተው ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማስቻላቸውንም ጠቁመዋል። ለአብነትም ወጣቶችና ሴቶች በእንስሳት ልማትና በእንስሳት ተዋጽኦ ምርት ላይ በመሰማራት ከራሳቸው ባለፈ ለሌሎችም የሥራ ዕድል እየፈጠሩ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የሕብረት ሥራ ሪፎሪም ትግበራ ከተጀመረ ወዲህ ማህበራት ምርትና አገልግሎታቸውን በማቅረብ ገበያ እያረጋጉ እንደሚገኙም ዳይሬክተሩ ጠቅሰዋል። እንደ አቶ ሳሙኤል ገለጻ፤ የሕብረት ሥራ ማህበራት ሪፎርም ማስጀመሪያ ንቅናቄ በማድረግ ወደ ሙሉ ትግበራ ከተገባ ወዲህ ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል። ይህንን አጠናክሮ ለማስቀጠልም ባለድርሻ አካላት ተግተው መስራት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።