ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
አዲስ አበባ እያስመዘገበች የምትገኘው ሁለንተናዊ ለውጥ ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት የሚሆን ነው
Jan 22, 2026 26
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ አዲስ አበባ ከተማ እያስመዘገበች የምትገኘው ሁለንተናዊ ለውጥ ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት የሚሆን ነው ሲሉ የተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ከንቲባዎች ገለጹ፡፡ በአዲስ አበባ የልማትና የገቢ አሰባሰብ እንቅስቃሴ ላይ ያላቸውን አድናቆትም ተናግረዋል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ሲካሄድ የቆየው የአሕጉራዊ የተሞክሮ ልውውጥ እና የድርጊት መርሃ-ግብር ግምገማ አውደ ጥናት ተጠናቅቋል። በአውደ ጥናቱ ላይ የተሳተፉ የአፍሪካ ከተሞች ከንቲባዎችና የስራ ኃላፊዎች በአዲስ አበባ ያለውን የልማት እንቅስቃሴና የዲጂታል የገቢ አሰባሰብ ስርዓት ተመልክተዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ከንቲባዎች ጋር በመሆን የአዲስ አበባ ገቢዎች ቢሮን የስራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል። በተጨማሪም የአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ከንቲባዎች የከተማዋን የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች ተዘዋውረው ተመልክተዋል። ተሳታፊዎቹ በጉብኝታቸው ወቅት በአዲስ አበባ የታዘቧቸው ተሞክሮዎች ለሀገሮቻቸው ትልቅ ትምህርት የሚሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የታንዛንያ ዳሬሰላም ከተማ ከንቲባ ኑረዲን ቢላለ፤ አዲስ አበባ ከተማ ራሷን በራሷ ለማስተዳደር የምታደርገውን ጥረት አድንቀው፤ ስለ አዲስ አበባ ከተማ አሁን በቂ ግንዛቤ አግኝቻለሁ ብለዋል። ከተማዋ ግብር የምትሰበስብበትንና ተግባራትን የምታከናውንበትን መንገድ መመልከታቸውን ጠቅሰው ከዚህም ሰፊ ልምድ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ ያገኙትን ተሞክሮዎች በዳሬሰላም ተግባራዊ እንደሚያደርጉም ጠቁመዋል፡፡   የሉሳካ ከንቲባ ቺላንዶ ቺታንጋላ አንዲት ከተማ ስኬታማ ለመሆን ጠንካራ የገቢ አሰባሰብ ስርዓት ሊኖራት እንደሚገባ ጠቅሰው፤ በአዲስ አበባ ያየነው የገቢ አሰባሰብ ስርዓትና ገቢ እንዳይባክን የሚደረጉ የፈጠራ ስራዎች የሚደነቁ ናቸው ከዚህም ብዙ ልምድ ቀስመናል ብለዋል።   የካሜሩን ያወንዴ ከተማ የበጀት ቢሮ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አሞዉጎ ብረቲንደ በበኩላቸው፤ በአዲስ አበባ የተመለከቱት የቴክኖሎጂ አጠቃቀም ድንቅ ነው ሲሉ ገልጸውታል። በተለይም በገቢ አሰባሰብ በኩል የተመለከቱት የቴክኖሎጂ አጠቃቀም በካሜሩን ሊተገበር የሚገባው ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ የከተሞች ትራንስፎርሜሽንን የልማት እቅዷ ማዕከል ማድረጓ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት አርአያ የሚሆን ነው
Jan 22, 2026 61
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የከተሞች ትራንስፎርሜሽንን የልማት እቅዷ ማዕከል ማድረጓ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት አርአያ የሚሆን ነው ሲሉ የቢግ ዊን ፊላንትሮፒ የከተሞች ከፍተኛ ዳይሬክተር ሄስቲንግስ ቺኮኮ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያን የከተሞች የትራንስፎርሜሽን ጉዞ ለማፋጠንና የከተሞችን የሀብት ማሰባሰብ አቅም ማሳደግ የሚያስችል ስልታዊ ስምምነት ተፈረመ። ስምምነቱን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር ከዓለም አቀፉ ተቋም ቢግ ዊን ፊላንትሮፒ (Big Win Philanthropy) ጋር በይፋ ተፈራርመዋል።   የቢግ ዊን ፊላንትሮፒ የከተሞች ከፍተኛ ዳይሬክተር ሄስቲንግስ ቺኮኮ በፊርማ ሥነ ስርዓቱ ላይ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የከተሞችን ትራንስፎርሜሽን የልማት እቅዷ ማዕከል ማድረጓ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ትልቅ አርአያነት ያለው ተግባር ነው። ኢትዮጵያ የከተሜነትን ሂደት በታቀደ ስልት እና በጠንካራ ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት እየመራች መሆኑ የሚደነቅ ነው ብለዋል። የአፍሪካ የወደፊት ዕጣ ፈንታ በከተሞች ስኬት ላይ የተመሰረተ መሆኑን ጠቁመው፤ ከተሞች ለዜጎቻቸው ለሚሰጧቸው አገልግሎቶች ስትራቴጂካዊ ኢንቨስትመንት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ምርታማነትን ማሳደግ፣ ጥራት ያለው መሠረተ ልማት ማቅረብ እንዲሁም ፍትሐዊና ተደራሽ አገልግሎቶችን ማረጋገጥ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ የያዘችው ጠንካራ የለውጥ መርሃ ግብር ውጤታማ እንዲሆን ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥርም ጠቁመዋል፡፡ ይህ አዲስ የተፈረመው ስምምነት የሀብት ማሰባሰብ፣ የፋይናንስ አስተዳደር እንዲሁም የትራንስፎርሜሽን ጉዞውን ማፋጠን በሚሉ ቁልፍ ጉዳዮች ላይ በትኩረት እንደሚሰራ ተመላክቷል፡፡
ኢትዮጵያ የማር ምርታማነትን ለማሳደግ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮች ተግባራዊ እያደረገች ነው
Jan 22, 2026 56
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የማር ምርታማነትን ለማሳደግ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮች ተግባራዊ እያደረገች መሆኑን ተገለጸ። የኢትዮጵያ ንብ ሀብት ማህበር እና የተባበሩት መንግስታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት(UNIDO) በንብ ሀብትና በማር ምርታማነት ዙሪያ የመከሩበት የውይይት መድረክ ተካሂዷል።   በመድረኩ የተገኙት የግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና አሳ ሀብት ዘርፍ የሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ግርማ ሙሉጌታ እንደተናገሩት፤ የማር ሀብትን በውጤታማነት ጥቅም ላይ ማዋል የሚያስችል የተሻሻለ አሰራር ተግባራዊ ተደርጓል። መንግስት ለግብርናው ዘርፍ የሰጠው ልዩ ትኩረት መነቃቃት መፍጠሩን ገልጸው፤ አምራቾች በቴክኖሎጂ የታገዘ አሰራርን እንዲከተሉ ምቹ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን ጠቁመዋል። ለዚህም ስኬት ከበለጸጉ ሀገራት ጋር የሚደረግ የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር፣ የልምድ ልውውጥ ስራዎች እንዲሁም የባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ተሳትፎ ወሳኝ ሚና እንዳላቸው አብራርተዋል። መድረኩ የማር ምርት ጥራትን በመጠበቅ ለውጭ ገበያ የሚቀርበውን ምርት ለማሳደግና ዘላቂ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ያለመ መሆኑም ጠቁመዋል።   በአፍሪካ ህብረት እና በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የተባበሩት መንግስታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት(UNIDO) ተጠሪ ስቴፍን ካግቦ በበኩላቸው፣ ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ እያስመዘገበች ያለው እድገት የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የግብርና ምርቶችን እሴት ጨምሮ ለማቅረብ የተገነቡት ሶስት የተቀናጁ የግብርና ምርት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ለዘርፉ ትልቅ ተስፋ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። እነዚህ ፓርኮች ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ የፈሰሰባቸውና ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል የፈጠሩ መሆናቸውን ጠቁመው፤ የውጭ ኢንቨስትመንት ፍሰትን በመሳብ በኩል ውጤታማ እንደሆኑ ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም በዘርፉ ስኬታማ ለመሆን ለሚፈልጉ ሌሎች ሀገራት እንደ ትልቅ የልምድ ምንጭ እያገለገሉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ኢትዮጵያ በማር ምርት ዘርፍ የጀመረቻቸው ስራዎች ውጤታማ እንደሚሆኑ ያላቸውን እምነት ገልጸው፤ የUNIDO እና የኢትዮጵያ መንግስት ቅንጅት ለሌሎች ሀገራትም አርአያ የሚሆን ተግባር ነው ብለዋል፡፡   የኢትዮጵያ ንብ ሀብት ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ ነጋሽ በቃና በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ማርን እሴት ጨምሮ ለውጭ ገበያ በማቅረብ በኩል መንግስት ለዘርፉ ምርታማነት ያመቻቸውን የፖሊሲና የአሰራር ድጋፎች በአግባቡ ለመጠቀም ዝግጁ መሆናቸውን አመላክተዋል። ማህበሩ በመንግስትና በግል አጋርነት የሚከናወኑ ተግባራት እንዲጠናከሩ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸው፤ ውይይቱ ለሀገሪቱ የማር ዘርፍ እድገት አዲስ አቅጣጫ ይጠቁማል ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ በዓለም የኢኮኖሚ ፎረም ላይ ንቁ ተሳትፎ እያደረገች ነው
Jan 22, 2026 54
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ አራተኛ ቀኑን በያዘው የዓለም የኢኮኖሚ ፎረም ላይ በገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ በተመራው ልዑክ አማካኝነት የነቃ ተሳትፎ እያደረገች ትገኛለች። ሚኒስትሩ የዓለም አቀፍ ጤና እና ፋይናንስ የወደፊት ዕጣ ፈንታን አስመልክቶም በቢልጌትስ አስተናጋጅነት ትላንት በተካሄደው ውይይት ላይ ተሳትፈዋል፡፡   ሚኒስትሩ በውይይቱ ወቅት እንደገለጹት ኢትዮጵያ የዲጂታል ቴክኖሎጂንና ሰው ሰራሽ አስተውሎት(AI) በመጠቀም፣ በተለይም በገጠሪቱ የሀገሪቱ ክፍሎች የጤና አገልግሎት ተደራሽነትን ለማስፋፋት እያደረገች ያለውን እድገት አብራርተዋል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት(AI) እና የጤና ስርዓቶችን ለማጠናከር፣ የሰዉ ሃይል ልማትን ለማበረታታትና የዲጂታል መሰረተ ልማትን ለማሳደግ የረጅም ጊዜ አጋርነት እና ዘላቂ ፋይናንስ እንዲኖርም ጥሪ አቅርበዋል። የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ “ከድንገተኛ የኢኮኖሚ ቀውስ ባሻገር ያሉ ኢኮኖሚዎች” በሚለው የውይይት መድረክ ላይም ጠንካራ የኢኮኖሚ መሰረት ለመገንባት የሚያስፈልጉ ቁልፍ አምዶችን ዘርዝረዋል፡፡   ከፎረሙ ጎን ለጎንም ከቢልጌትስ እና ከአውሮፓ ህብረት የዓለም አቀፍ አጋርነት ኮሚሽነር ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አድርገዋል። ይህም ኢትዮጵያ ለፈጠራ፣ ለአጋርነት እና ለዘላቂ ልማት ያላትን ቁርጠኝነት ዳግም ያረጋገጠ ነው።   እስከ አሁን ያለው የኢትዮጵያ የዓለም የኢኮኖሚ ፎረም 2026 ተሳትፎ፣ ሀገሪቱ ዘላቂና ሁሉን አቀፍ እድገት ለማምጣት ፈጠራን፣ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንንና ስትራቴጂካዊ አጋርነትን ለመጠቀም ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑም ተገልጿል።
ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የመንግሥት የልማት ድርጅቶችን ወደ ላቀ ውጤታማነት አሸጋግሯል
Jan 22, 2026 64
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018 (ኢዜአ)፦የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የመንግሥት የልማት ድርጅቶችን ወደ ላቀ ውጤታማነት ማሸጋገሩን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ መለሠ መና ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት የሀገሪቱን ቁልፍ የመንግሥትና ሌሎች የፋይናንስ ተቋማትን ያሰባሰበው “የፋይናንስ እመርታ በኢትዮጵያ” ኮንፈረንስ መካሄዱ ይታወሳል። በኮንፈረንሱም በኢትዮጵያ ኢንቨትመንት ሆልዲንግስ ስር የሚገኙ የልማት ድርጅቶች የነበረባቸውን የፋይናንስ፣ የኦዲት፣ የካፒታል፣ የብድር ጫና እና የኮርፖሬት አስተዳደር ችግር በመቅረፍ ዘመናዊ የባለቤትነት፣ የአስተዳደር ስርዓት እና ዓለም አቀፍ የኮርፖሬት አስተዳደር ስርዓት እንደተዘረጋላቸው ተገልጿል። ዘመናዊ የኦዲት ስርዓት እንዲከተሉ መደረጉን እና ይህም ካጋጠማቸው የኢኮኖሚ ስብራት ወጥተው በፍጥነት ውጤታማ እንዲሆኑ አስቸሏል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ መለሠ መና ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ከ40 በላይ የመንግስት ልማት ድርጅቶች መኖራቸውን ተናግረዋል። ቋሚ ኮሚቴው ድርጅቶቹን ከተሰጣቸው ተልዕኮና ስትራቴጂካዊ ዕቅድ አንጻር የመከታተል፣ የመቆጣጠርና የመደገፍ ስራ በማከናወን ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በለውጡ መንግሥት የተደረገውን ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም ተከትሎ የልማት ድርጅቶች ከነበሩበት ኪሳራ ወጥተው ወደ ትርፋማነት መሸጋገራቸውን አንስተዋል። የልማት ድርጅቶቹ ተኪ ምርት በማምረት ከውጭ የሚገባ ምርት መጠን እንዲቀንስ፣ ኢንቨስትመንት እንዲስፋፋ እና ለዜጎች የስራ እድል እንዲፈጠር በማድረግ ረገድ ትልቅ ሚና እያበረከቱ ነው ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅትም ለሀገር ኢኮኖሚ እድገት እና ለቀጣይ ትውልድ መሸጋገር የሚችል ሃብት በመፍጠርና በማፍራት ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል፡፡   የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሀብታሙ ኃይለሚካኤል በበኩላቸው፣ ከለውጡ በፊት አብዛኛዎቹ የልማት ድርጅቶች ዘመናዊ አሰራርን ባለመከተላቸው ለኪሳራ ተዳርገው መቆየታቸውን አስታውሰዋል። የለውጡ መንግስት የተከተለው ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ድርጅቶቹ ያለባቸውን ዕዳ በማቃለልና ከኪሳራ እንዲወጡ በማድረግ በዘርፉ ተጨባጭ ለውጦችን አምጥቷል ነው ያሉት፡፡ በዚህም ድርጅቶቹ የሃብት አማራጮችን በማስፋት በኢኮኖሚ እድገት ውስጥ ጉልህ ሚና ለመጫወት ትኩረት ሰጥተው በመስራት ላይ ይገኛሉ ብለዋል ፡፡ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ ሥር የሚተዳደሩ የልማት ድርጅቶች ከአጠቃላይ ሀገራዊ ምርት ውስጥ የ12 በመቶ ድርሻ ያላቸው ሲሆን ከፍተኛ ታክስ ከፋዮች መሆናቸውን አንስተዋል። ለአብነትም በ2017 በጀት ዓመት ከ228 ቢሊዮን ብር በላይ ለመንግስት ታክስ መክፈላቸውን ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚው ጠቅሰዋል።    
በሐረሪ ክልል፣ ምስራቅ ሐረርጌ ዞንና ማያ ከተማ አስተዳደር ከ11ሺህ በላይ ከሆኑ የኢኮኖሚ ድርጅቶች መረጃ ይሰበሰባል
Jan 22, 2026 253
ሐረማያ ፤ጥር 14/2018 (ኢዜአ) ፡-በሐረሪ ክልል፣ ምስራቅ ሐረርጌ ዞንና ማያ ከተማ አስተዳደር ከ11ሺህ በላይ ከሆኑ የኢኮኖሚ ድርጅቶች መረጃ የመሰብሰብ ስራ ይከናወናል። በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የሐረር ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ለሚያከናውኑ የመስኩ ባለሙያዎች ስልጠና እየሰጠ ነው። በአገልግሎቱ የሐረር ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ሙክታር ጀማል እንደገለጹት ስልጠናው ከሐረሪ ክልል፣ ምስራቅ ሐረርጌ ዞንና ማያ ከተማ አስተዳደር ለተውጣጡ 625 መረጃ ሰብሳቢዎች፣ ተቆጣጣሪዎች እና አስተባባሪዎች እየተሰጠ ነው።   በሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ ለ10 ቀናት በሚሰጠው በዚሁ ስልጠና በሶስት የተለያዩ ክፍሎች ላይ ያተኮረ ሙያዊ ስልጠና እንደሚሰጥ ጠቁመዋል። በዚህም በሐረሪ ክልል፣ ምስራቅ ሐረርጌ ዞንና ማያ ከተማ አስተዳደር ከተመረጡ 11ሺህ 567 የኢኮኖሚ ድርጅቶች የሰው ሃይላቸውን፣ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴያቸውንና ወጪና ገቢያቸውን ጨምሮ ሌሎችም መረጃዎች ይሰበሰባሉ ብለዋል። እንደ አቶ ሙክታር ገለጻ ከጥር 25 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ዋናው የመረጃ መሰብሰብ ስራ እንደሚገባም አክለዋል። የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ዘርፈ ብዙና የተለያዩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥናቶችን በማከናወን መረጃዎችን በመሰብሰብ ይተነትናል ያሉት ደግሞ የስልጠናው ዋና አስተባባሪ አቶ እንዳሻው ፈለቀ ናቸው።   ስልጠናው የኢኮኖሚ ድርጅቶችን መረጃ ለመሰብሰብ የሚያስችሉ ግንዛቤን ለቆጣሪዎች በመስጠት ስራውን ለማሳካት ያለመ ነው ብለዋል። የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራም የአገራችንን የኢኮኖሚ ሃብት ደረጃ ለማወቅ እንዲሁም ድርጅቶች ያላቸውን የሰው ሃይልና ሌሎች መረጃዎቻቸውን ለመለየትና ለጥናትና ምርምር፣ ለፖሊሲ ዝግጅት በማዋል ዘርፈ ብዙ ጥቅም አለው ብለዋል።   ስልጠናውን እየተከታተሉ ከሚገኙት መካከል ማዓዛ ሀብታሙ እንደገለጸችው ስልጠናው የጠራ መረጃ በመሰብሰብ ለአገራዊ እድገት መሰረት እንዲጣል የሚያግዝ ነው ብላለች። ስልጠናው በኢኮኖሚው ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት ለማስቀጠል ፋይዳው የጎላ ነው ያለው ደግሞ ሌላው ሰልጣኝ ሸምሸዲን አብዶ ነው።      
የኢትዮጵያ ከተሞችን የብልጽግና ማዕከል በማድረግ ምቹ የከተሜነት ምኅዳር የመፍጠር ጥረት ውጤታማ እየሆነ ነው
Jan 22, 2026 207
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ከተሞችን የብልጽግና ማዕከል በማድረግ ለነዋሪዎች ምቹ የከተሜነት ምኅዳር የመፍጠር ጥረት ውጤታማ እየሆነ መምጣቱን የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ።‎ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር እና ቢግ ዊን ፊላንትሮፒ የኢትዮጵያን ከተሞች የብልጽግና ተምሳሌት የማድረግ የመሠረተ ልማት ግንባታ ርዕይ የሚደግፍ የትብብር ስምምነት ተፈራርመዋል። በዚሁ ወቅት የኢትዮጵያ ከተሞችን የትራንስፎርሜሽን ጉዞ የሚያሳልጥ የከተሞች ገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር ይፋ ሆኗል።   በዚሁ ወቅት የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ፤ የኢትዮጵያ ከተሞች መስፋፋት በኢኮኖሚ ዕድገትና በሥራ ዕድል ፈጠራ ወሳኝ የሃብት ምንጭነት እያገለገሉ ነው ብለዋል። የከተሜነት ምኀዳሩ ለነዋሪዎች ምቹ የማድረግ ጥረትም የዜጎችን ኑሮ በማሻሻል ተወዳዳሪ የኢኮኖሚ አቅም ለመገንባት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል። አዲሱ የከተሞች የገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብርም የከተሞችን የመሠረተ ልማትና መሠረታዊ አገልግሎቶች በራስ የገቢ አቅም የሚደግፉበትን ሥርዓት እንደሚፈጥር ተናግረዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የንብረት ታክስ አስተዳደር ሥርዓቱን በማዘመን የከተሞችን ገቢ የማመንጨት አቅም የሚያሻሽል ብሔራዊ የካዳስተር፣ የመሬት ሊዝና የንብረት ታክስ አሰራር መፈጠሩን አንስተዋል። በብድር፣ በመንግሥትና በግል አጋርነት አማካኝነት የግሉ ዘርፍ የከተሞችን የመሠረተ ልማት ግንባታ የሚደግፍበት የፋይናንስ አቅርቦት ሥርዓት መገንባቱንም አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ከተሞችን የብልጽግና ማዕከል በማድረግ ለነዋሪዎች ምቹ የከተሜነት ምኅዳር የመፍጠር ጥረት ፍሬ እያፈራ ነው ያሉት ሚኒስትሯ፤ ከተሞችን ለአፍሪካ ከተሞች አርዓያ የማድረግ ጥረትም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የኢትዮጵያ ከተሞች የትራንስፎርሜሽን ገቢ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብር በስኬት ለመምራትም ከክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ጋር በቅርበት የሚሰራ የቴክኒክ ቡድን እንደሚዋቀር አብራርተዋል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ባለፉት ስድስት ወራት በልማትና መልካም አስተዳደር ዘርፎች ስኬታማ ተግባራት ተከናውነዋል
Jan 22, 2026 79
አሶሳ፤ ጥር 14/2018(ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ባለፉት ስድስት ወራት በልማትና መልካም አስተዳደር ዘርፎች ስኬታማ ተግባራት መከናወናቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ።   የክልሉ መንግስት የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት አፈጻጸም ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት እየተገመገመ ነው። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ ቃሲም ኢብራሂም የክልሉን መንግስት የስድስት ወራት አፈጻጸም ሪፖርት በዝርዝር አቅርበዋል። በሪፖርታቸውም ባለፉት ስድስት ወራት በክልሉ የገቢ አሰባሰብ ስርዓቱን በማዘመን 5 ቢሊዮን 194 ሚሊዮን ብር መሰብሰቡንና 4 ሺህ 158 ኪሎ ግራም ወርቅ ወደ ብሔራዊ ባንክ መግባቱን በተሻለ አፈጻጸም አንስተዋል።   ይህም በክልሉ እየተከናወኑ ላሉ ዘርፈ ብዙ የልማት ፕሮጀክቶች ማስፈፀሚያ እና ለሌሎችም የልማት ተግባራት ተጨማሪ አቅም ለመፍጠር እንደሚያስችል አንስተዋል። በመድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተደድር አሻድሊ ሀሰን፤ ባለፉት ስድስት ወራት ከክልሉ ገቢ የመሰብሰብ አቅም ጋር የተመጣጠነ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። በክልሉ የኢንቨስትመንት አቅሞችን በማልማት የህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ተግባራት በሰፊው እየተተገበሩ መሆኑን አንስተው፤ ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።   በቴክኖሎጂ የታገዘ የአገልግሎት አሰጣጥን በማስፋት ዜጎች የተቀላጠፈ አገልግሎት እንዲያገኙ እና ብልሹ አሰራሮችን ለማስቀረት የሚያስችሉ ተግባራትም ተከናውነዋል ብለዋል። በከተማ እና በገጠር እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት በላቀ የህዝብ ተሳትፎ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው፥ በሌማት ትሩፋት እና ሌሎች የልማት ኢንሼቲቮችም ቀጣይነት ያለው ውጤት እየተመዘገበባቸው መሆኑን አንስተዋል። ባለፉት ስድስት ወራት የተከናወኑትን የልማት እና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ፍጥነትና ፈጠራ በታከለበት መንገድ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ነው የገለጹት።  
በከተማዋ የቱሪስት ፍሰትና የቆይታ ጊዜን የሚያሳድጉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ ነው
Jan 22, 2026 92
ባህር ዳር፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦ በባህር ዳር ከተማ የቱሪስት ፍሰትን ለመጨመርና የቆይታ ጊዜን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ባህል ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ገለጸ። በባህር ዳር ከተማ ጣና ሃይቅ ለ9ኛ ዙር የታንኳ ቀዘፋ ውድድርና የጀልባ ትርኢት እየተካሄደ ይገኛል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ባህል ቱሪዝምና ስፖርት መምሪያ ሃላፊ አቶ ጋሻው እንዳለው እንደገለጹት፤ "የጥርን በባህር ዳር" መርሃ ግብር ልዩ ልዩ ኹነቶች የከተማዋን የቱሪዝም እንቅስቃሴ እያሳደገው ይገኛል።   የዚሁ አካል የሆነው የጣና ላይ የታንኳ ቀዘፋ ውድድር እና የጀልባ ትርኢት የከተማዋን የቱሪስት ፍሰት ለማሳደግና የቆይታ ጊዜን ለማራዘም ማገዙንም አክለዋል። "ጥርን በባህር ዳር " አካል የሆነው በጣና ላይ የሚከናወነው የታንኳ ቀዘፋ ውድድር ተጨማሪ የቱሪስት መስህብ እየሆነ መጥቷል ብለዋል። ከተማ አስተዳደሩ የቱሪስቱን ፍሰት በመጨመርና የዘርፉን አቅም ለማሳደግ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን መደገፍ እንዲሁም የኮሪደር ልማት ማከናወኑን አንስተዋል።   የባህር ዳር ከተማን የቱሪስት ፍሰት በመጨመርና የዘርፉን አቅም ለማሳደግ መሰል ተግባራት በስፋት እየተከናወኑ መሆናቸውንም ተናግረዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የባህር ዳር ከተማ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ሃላፊ ብርሃን ንጉሴ በበኩላቸው፤ የከተማዋን ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች በፍጥነትና በጥራት በማከናወን ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል።   በተለይም የኮሪደር ልማት ስራዎች የባህር ዳር ከተማን ለኑሮ፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ ማድረጋቸውን ገልፀዋል። "ጥርን በባህር ዳር" መርሃ ግብር አካል የሆነው የጣና ላይ የታንኳ ቀዘፋ ውድድር እና የጀልባ ትርኢት የከተማዋ የቱሪዝም ዘርፍ ወደ ላቀ ደረጃ እንዲያድግ ማገዙን ጠቁመዋል። ውድድሩን ይበልጥ በማስተዋወቅ ተጨማሪ የቱሪስት መስህብ ለማድረግና የመንግስታቱ ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስ እና ባህል ተቋም (ዩኔስኮ) እንዲመዘገብ ሁላችንም የሚጠበቅብንን መስራት ይገባል ብለዋል። በውድድር ስነ ስርዓቱ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችና የከተማው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
የአዲስ አበባ ስኬታማ የለውጥ እርምጃዎች መዲናዋን ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት ያደረጉ ናቸው
Jan 22, 2026 84
አዲስ አበባ፤ጥር 14/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማ ስኬታማ የለውጥ እርምጃዎች ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን በማሳደግ መዲናዋን ለአፍሪካ ከተሞች ተምሳሌት ያደረጉ መሆናቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። አሕጉራዊ የተሞክሮ ልውውጥ እና የድርጊት መርሃ-ግብር የሂደት ግምገማ አውደ ጥናት በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ይገኛል።   በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) ድጋፍ የተካሄደው የአፍሪካ ከተሞች የፋይናንሻል ማኔጅመንት አፈፃጸም የዳሰሳ ጥናት ውጤት በመድረኩ ላይ ይፋ ሆኗል። በአዲስ አበባ፣ናይሮቢ፣ ዳሬሰላም፣ ሉሳካ፣ ኪጋሊ እና በያውንዴ የአፍሪካ ከተሞች በተካሄደው የዳሰሳ ጥናት ውጤት አዲስ አበባ ከተማ በላቀ አፈፃጸም ቀዳሚ መሆኗ ተገልጿል። በዳሰሳ ጥናቱ ከተካተቱ ስድስት ዋና ዋና መመዘኛዎች መካከል አዲስ አበባ በአምስት አመላካቾች ከፍተኛ ውጤት በማስመዝገብ የተሻለ ገቢና የፋይናንስ ሃብት አስተዳደር ስኬታማ ከተማ መሆኗ ተመላክቷል። በዚሁ ጊዜ የተገኙት የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ የመዲናዋን ፈጣን የዕድገት ጉዞ የሚያሳልጡ ስኬታማ የሪፎርም እርምጃዎችን በመውሰድ በቁርጠኝነት መተግበራቸውን ገልጸዋል።   የንግድ ፈቃድ አሰጣጥና የገቢ አሰባሰብ ሥርዓቱንም በዲጂታል ቴክኖሎጂ በማዘመንና ግልጸኝነትን በማስፈን በራስ አቅም የልማት ኢንቨስትመንትን የምትደግፍበት ምኅዳር መፍጠር እንደተቻለ ተናግረዋል። የአመራር ቁርጠኝነት፣ ሥራን በዕውቀትና ቴክኖሎጂ መደገፍ እንዲሁም በመንግስትና ህዝብ መካከል ግልጸኝነትን መፍጠር ለከተሞች ትራንስፎርሜሽን መሠረታዊ ጉዳዮች መሆናቸውን አስረድተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ስትራቴጂክ የሪፎርም እርምጃዎችም የመዲናዋን ሁለንተናዊ ተወዳዳሪነት በማሳደግ ለአፍሪካ ከተሞች ጭምር የለውጥ ተምሳሌት ያደረጉ መሆናቸውን አብራርተዋል።   የከተሞች የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚወሰነው ዛሬ በሚዘረጋ ጠንካራ የፋይናንስ ሥርዓት ነው ያሉት ከንቲባ አዳነች፤ ለዚህም የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ለከተማ የሪፎርም ሥራ የሚያደርገው እገዛ የሚደነቅ ነው ብለዋል። በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን የፆታ፣ የድህነት እና የማህበራዊ ፖሊሲ ዳይሬክተር ዙዛና ብሪክሲዮቫ ሽዊድሮቭስኪ እንዳሉትም የፕሮጀክቱ ዓላማ የማዘጋጃ ቤት የፋይናንስ አቅምን ማጠናከር እና ዘላቂ የፋይናንስ መቋቋም አቅምን ማሳደግ ነው ብለዋል። ኤኒሼቲቩ ስድስት የአፍሪካ ከተሞችን ማለትም አዲስ አበባ፣ ዳሬሰላም፣ ኪጋሊ፣ ናይሮቢ፣ ሉሳካ እና ያውንዴን እንደሚደግፍም ጠቁመዋል። የናይሮቢ ከተማ ካውንቲ ምክትል ገዥ ጀምስ ንጆርጅ በበኩላቸው ጉባኤው ለከተሞች እድገት ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው ብለዋል። በታንዛኒያ የጌሊላ ከተማ ከንቲባ ኖርዲን ቤላል እንዳሉትም ውይይቱ ከተሞች የራሳቸዉን ስራዎች እንዲተገብሩ የሚያደርግ ነዉ ብለዋል። በመድረኩ የተገኙ የበርካታ አፍሪካ ሀገራት ከተሞች ከንቲባዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላትና ተሳታፊዎችም የአዲስ አበባ ከተማ በልማት ሥራዎች ላይ ያስመዘገበቻቸውን ስኬቶች በተሞክሮነት ተመልክተዋል።  
በሕገወጥ ንግድ ላይ በተሰማሩ ከ133 ሺህ በላይ የንግድ ተቋማት ላይ እርምጃ ተወስዷል
Jan 22, 2026 74
ደሴ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦በ2018 በጀት ዓመት ስድስት ወራት በሕገ-ወጥ ንግድ ላይ በተሰማሩ ከ133 ሺህ በላይ የንግድ ተቋማት ላይ እርምጃ መወሰዱን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለጹ። የሚኒስቴሩ የ2018 ግማሽ ዓመት የሥራ አፈጻጸም ግምገማና የሴክተር ጉባኤ በደሴ ከተማ እየተካሄደ ነው።   የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፣ ተቋማቸው ባለፉት ስድስት ወራት ገበያ በማረጋጋት፣ ህገ ወጥ ንግድን በመቆጣጠርና የወጪ ንግድን ለማሳደግ በትኩረት ሲሰራ ቆይቷል። ገበያን ለማረጋጋት የገበያ ማዕከላትን ለማስፋትና ደረጃቸውን ለማሻሻል የተደረጉ ጥረቶችም ተጨባጭ ውጤት ማስገኘታቸውን ተናግረዋል። በዚህም የኑሮ ውድነትንና የዋጋ ግሽበትን ወደ ነጠላ አሃዝ ዝቅ ማድረግ መቻሉ አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል። ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የተለያዩ እርምጃዎች መወሰዳቸውን ነው የገለጹት። በበጀት ዓመቱ ሰድስት ወራት በሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴ ላይ በተሰማሩ ከ133 ሺህ በላይ የንግድ ተቋማት ላይ እርምጃ መወሰዱን ለአብነት በማንሳት። በሀገሪቱ ጤናማ የንግድ ሥርዓት በመፍጠር ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የወጪ ንግዱን ለማሳለጥ በተደረገ ጥረትም ባለፉት ስድስት ወራት ወደ ውጭ ከተላኩ ምርቶች ከ5 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ መገኘቱን ጠቅሰዋል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ አህመዲን መሀመድ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ በክልሉ ህገ ወጥ ንግድን ለመቆጣጠርና ገበያን ለማረጋጋት በተሰራው ስራ ውጤት መመዝገቡን አንስተዋል። ሁለገብ ዘመናዊ የገበያ መሰረት ልማት በመገንባት ውጤታማ የንግድ ሥርዓት ለመፍጠር የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ ኃላፊ ባዩሽ ተስፋዬ (ዶ/ር)፣ በክልሉ ገበያን በማረጋጋትና ጤናማ የንግድ ውድድር መፍጠር የሚያስችሉ አሰራሮች ተግባራዊ መደረጋቸውን ገልጸዋል። በመድረኩ የፌዴራል፣ የክልልና የተጠሪ ተቋማት አመራሮችና ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።
የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግርን ለማፋጠን ያግዛል
Jan 22, 2026 85
ሮቤ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ በዘርፉ የተገኙ ስኬቶችን ለማስቀጠልና የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግርን ለማፋጠን አጋዥ መሆኑን የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት አስታወቀ። አገልግሎቱ በተለያዩ የሀገሪቷ አካባቢዎች በሚካሄደው 2ኛው ዙር የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ ላይ ለሚሰማሩ ባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ስልጠና መስጠት ጀምሯል። የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የቴክኒክ አስተባባሪ ለሊሳ በሾ፣ በስልጠናው መክፈቻ ባደረጉት ንግግር፣ የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ መካሄድ ውሳኔ ሰጪ አካላት ጥራት ያለውና መረጃን መሰረት ያደረገ ውሳኔ እንዲያሳልፉ ያግዛል።   በቆጠራው በመላው አገሪቱ የሚገኙ ከፍተኛ፣ መካከለኛና ዝቅተኛ ኢንተርፕራይዞች የሚካተቱ ሲሆን ቆጠራው በሁሉም ከተሞች ቤት ለቤት በመዞርና በገጠር ናሙና በመውሰድ ይከናወናል ብለዋል። የኢኮኖሚ ድርጅቶቹ ቆጠራ በዘርፉ የተገኙ ስኬቶችን ለማስቀጠልና የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግርን ለማፋጠን እንዲሁም የፖሊሲ አማራጭ ሃሳቦችን ለማመንጨት ጉልህ ሚና እንዳለው አመልክተዋል። ለኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራው የሚሳተፉ ከኦሮሚያ ክልል ከባሌ፣ ምሥራቅ ባሌ፣ምዕራብ አርሲ፣ምሥራቅ ቦረና እንዲሁም ከሶማሌ ክልል ሊበን ዞኖች የተወጣጡ 734 የዘርፉ ባለሙያዎች ስልጠናው የሚሰጥ መሆኑን አንስተዋል። ቆጠራው በዘርፉ ለሚዘጋጁ እቅዶች፣ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች ትክክለኛ ግብዓት ለማግኘት እንደሚያስችል ጠቅሰው፣ የስልጠናው ተሳታፊዎችም የአቅም ግንባታ ስልጠናውን በአግባቡ በመከታተል ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።   በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የባሌ ጎባ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሽመልስ አሰፋ በበኩላቸው፣ ስልጠናው መረጃ ሰብሳቢዎች ጥራትና ወቅቱን የጠበቀ ተዓማኒነት ያለው መረጃ መሰብሰብ የሚችሉበትን ክህሎት እንዲያገኙ ያግዛል ብለዋል። የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራው በመላው ኢትዮጵያ ከመስከረም 2018 ጀምሮ መካሄድ መጀመሩ ይታወቃል።
በዞኑ የፍራፍሬ ልማትን ለማስፋት የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ ነው
Jan 22, 2026 59
መቱ ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦በኢሉአባቦር ዞን በኢኒሼቲቭ መልክ እየተተገበረ የሚገኘውን የፍራፍሬ ልማት ለማስፋት የችግኝ ዝግጅት በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የኢሉአባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቻላቸው አዱኛ፣ በዞኑ በኢኒሼቲቭ መልክ አቮካዶ፣ ሙዝና ፓፓያ በስፋት እየለማ ይገኛል ብለዋል። በዞኑ ከ32 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት ላይ የፍራፍሬ ልማት እየተከናወነ ሲሆን ከሚለማው መሬት ውስጥ 28 ሺህ ሔክታር ላይ የሚገኘው ምርት መስጠት መጀመሩን ገልጸዋል።   ስራውን የበለጠ ለማፋፋትም በ220 የመንግስት የችግኝ ጣቢያዎችና በአርሶ አደሮች ማሳ ላይ የችግኝ ዝግጅት እየተካሄደ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም ምርታማነታቸው ከፍተኛ የሆኑ ከግብርና ምርምር የወጡ የአቮካዶ፣ የሙዝና የሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች የተዘጋጁ መሆናቸውን ነው የገለጹት። በችግኝ ማፍላት ስራው ከ42 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በመሳተፍ ላይ መሆናቸውንም አክለዋል። በበጋው ወራት የተዘጋጁት እነዚህን ችግኞች በተቀናጀ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ በተሰራበት መሬት ላይ እንደሚተከሉም ገልጸዋል።   ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ የሚሰጡት እነዚህ ችግኞች የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እንደሚያግዙም አስረድተዋል። ጥምር ጥቅም በሚሰጡ ችግኝ ማፍላት ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል በዞኑ በሁሩሙ ወረዳ የሎኮ ሳያ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ተካልኝ ታደገ እንዳሉት፤ አቮካዶና ሙዝ በማምረት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ ነው።   ስራውንም የዛሬ ሁለት ዓመት በበጋ ወራት በተቀናጀ የተፋሰስ ልማት በተከናወነባቸው ሩብ ሔክታር መሬታቸው ላይ በመተግባር መጀመራቸውን አስታውሰዋል። የፍራፍሬ ግብርናው በትንሽ ማሳ ላይ የምግብ ዋስትናና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ አቅም እንደሆናቸው አንስተዋል።
በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ አሠራር መተግበሩ የተሻለ ገቢ እንዲሰበሰብ አስችሏል
Jan 22, 2026 139
ነገሌ ቦረና፤ ጥር 14/2018 (ኢዜአ)፡- የግብር ከፋዩ ግንዛቤ በማደጉና በዲጂታል ቴክኖሎጂ የታገዘ አሠራር በመተግበሩ የተሻለ ገቢ መሰብሰቡን የምሥራቅ ቦረና ዞን ገቢዎች ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። በጽሕፈት ቤቱ የዕቅድ፣ በጀት ክትትልና ግምገማ ባለሙያ መዓዛ አሊ እንዳሉት፤ ገቢ የመሰብሰብ ዐቅምን አሟጦ ለመጠቀም የግብር ከፋዩን ግንዛቤ የማሳደግ ሥራ በትኩረት ሲሠራ ቆይቷል። የገቢ አሰባሰቡን በዲጂታል ቴክኖሎጂ እንዲታገዝ መደረጉም የገቢ ዐቅምን ማሳደግ ማስቻሉን ገልጸው፤ በበጀት ዓመቱ የመጀመሪያ አጋማሽ ከ854 ሚሊየን 528 ሺህ ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን ጠቅሰዋል። አፈጻጸሙ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ341 ሚሊየን 502 ሺህ ብር ብልጫ እንዳለውም ለኢዜአ ተናግረዋል። በነገሌ ቦረና ከተማ በሆቴል ንግድ የተሰማሩት አመለወርቅ ክፍሌ እንዳሉት፤ ዐቅምን ያገናዘበ የግብር ውሳኔ መሰጠቱ ነጋዴው ግብሩን ያለቅሬታ እንዲከፍልና ዜጎች የተሟላ መንግሥታዊ አገልግሎት እንዲያገኙ አስችሏል።   በሸቀጣ ሸቀጥ ንግድ ሥራ የተሰማሩት ቢኒያም ተፈራ በበኩላቸው፤ ግብርን በወቅቱ በመክፈል ሕግና ሥርዓትን ማክበር እንዲሁም ፍትሐዊ የንግድ ውድድርን ማስፈን የነጋዴው ግዴታ መሆኑን አስገንዝበዋል።   የሀገር ልማትን ለማስቀጠል ግብር የመክፈል ግዴታ የተጣለበት ዜጋ ሁሉ ኃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባ ያስረዱት ደግሞ ሌላኛዋ ግብር ከፋይ ብርቅነሽ ገብረሚካኤል ናቸው።   በታማኝነት ግብር በመክፈል ሕገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ማስቆምና የሕግ የበላይነትን የማስከበር ኃላፊነታችንን እንወጣለን ሲሉም አስተያየት ሰጭዎቹ በአጽንኦት ገልጸዋል።
የግብይት ማዕከላትን ደረጃ የማሻሻል ሥራ እየተከናወነ ነው-ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)
Jan 22, 2026 78
ሆሳዕና፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦ገበያን ለማረጋጋትና ህገወጥ ንግድን ለመቆጣጠር የሚረዱ የግብይት ማዕከላትን ከማስፋት ባለፈ ደረጃቸውን የማሻሻል ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለፁ። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ሚኒስቴሩ ገበያን ለማረጋጋትና ህገወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመቆጣጠር የሚረዱ የግብይት ማዕከላትን ከማስፋፋት ባለፈ ደረጃቸውን የማሻሻል ሥራ በመላ ሀገሪቱ እያከናወነ ይገኛል።   ቀደም ሲል ማህበረሰቡ በሚፈለገው ልክ የግብይት ማዕከላት ባለመስፋፋታቸው የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመሸመት አስቻይ ሁኔታዎች እንዳልነበሩ አስታውሰዋል፡፡ የንግድ ስርዓቱን ለማዘመንና የግብይት ማዕከላትን ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቷል   ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ችግሩን በመፍታት ገበያውን ለማረጋጋት በተሰራው ሥራ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ1ሺህ 900 በላይ የቅዳሜና እሁድ የግብይት ማዕከላትን ማቋቋም ስለመቻሉም ተናግረዋል፡፡ በንግድ ሥርዓቱ ሲስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን ለመፍታት የገበያ ማዕከላትን ከማስፋፋት ባለፈ ደረጃቸውን የማሻሻልና የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውንም ገልጸዋል።   የግብይት ማዕከላቱ ጤናማ የንግድ ስርዓትን ለማሳለጥና ገበያን ለማረጋጋት ሚናቸው የጎላ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ማዕከላቱን በመሰረተ ልማት የማጠናከር ሥራ መጀመሩንም ተናግረዋል። ይህም በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ምርቶችን ለማህበረሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ ማስቻሉን አስረድተዋል። ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ በማድረግ ህዝብን ለጉዳት ሲዳርጉ የነበሩ አካላትም በህግ ተጠያቂ እንዲሆኑ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉንም ነው ሚኒስትሩ ያስታወቁት። በተከናወኑ የቁጥጥርና መሰል ሥራዎች የዋጋ ግሽበቱን መቀነስ እንደተቻለ ጠቁመው ተግባሩን የማጠናከር ሥራ በልዩ ትኩረት እንደሚመራም አመልክተዋል።
የገጠር መንገድ ግንባታው የአርሶአደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የበለጠ የሚያረጋግጥ ነው
Jan 22, 2026 203
ሐረር ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል እየተከናወነ ያለው የገጠር መንገድ ግንባታ የአርሶአደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የበለጠ ለማረጋገጥ ጉልህ ፋይዳ እንዳለው የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ዑመር ገለጹ። በሐረሪ ክልል ገጠሩን ከከተማ የሚያስተሳስር የ150 ኪሎ ሜትር የመንገድ ግንባታና ጥገና እየተከናወነ ይገኛል።   የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር ለኢዜአ እንዳሉት፣ የገጠር መንገድ ግንባታው፣አርሶአደሩ ምርቱን በቀላሉ ወደ ገበያ እንዲያቀርብ ያግዛል። የአርሶአደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የበለጠ ለማረጋገጥ የጎላ ሚና እንደሚኖረውም አንስተዋል። በክልሉ የኢንቨስትመንት ፍቃድ የወሰዱ አልሚዎች የስራ እንቅስቃሴን በጥብቅ ዲሲፕሊን መምራት ይገባል በከተማዋ እየተከናወነ ያለውን የኮሪደር ልማት ከገጠሩ ጋር በማስተሳሰር ሞዴል የገጠር መንደሮችን ለመገንባት እየተደረገ ያለውን ጥረት እንደሚያግዝም ነው ያነሱት። የክልሉ ትራንስፖርትና መንገድ ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊ ፈቲህ ተውፊቅ በበኩላቸው፣ በተያዘው በጀት ዓመት በክልሉ ገጠርን ከከተማ የሚያስተሳስሩና የህብረተሰቡን ኑሮ የሚያሻሽሉ የመንገድ መሰረተ ልማቶች እየተከናወኑ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   የአዳዲስ የገጠር መንገዶች ግንባታን ጨምሮ ነባሮቹን የማሻሻልና ሥራ በተያዘለት የጊዜ ገደብ በጥራት እንዲጠናቀቅም ድጋፍና ክትትል እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ የመንገዱ ግንባታ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እንደሚሰጣቸው ገልጸው፤ ለግንባታው አስፈላጊውን ትብብር እንደሚያደርጉ አረጋግጠዋል።   ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል የድሬ ጠያራ ወረዳ ሲጊቻ ቀበሌ ነዋሪ ሐሰን ዩስፌ፤ ምርታቸውን ከተማ ይዘው በመሄድ እንዲገበያዩና የተሻለ ጥቅም እንዲያገኙ የመንገዱ ግንባታ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።   ፉአድ ሙሳ በበኩላቸው፤ቀደም ሲል የነበረው መንገድ ጠባብና ለተሽከርካሪ ምልልስ አስቸጋሪ እንደነበር አስታውሰው፤ አዲስ እየተገነባ ያለው መንገድ ይህን ችግር በማቃለል የተሽከርካሪ ፍሰቱን ያሳልጣል ብለዋል።
የአዳማ-አዋሽ የፍጥነት መንገድ ፕሮጀክት በፍጥነት ሊጠናቀቅ ይገባል-ቋሚ ኮሚቴው
Jan 21, 2026 88
አዲስ አበባ፤ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦ የአዳማ-አዋሽ ምዕራፍ አንድ የፍጥነት መንገድ ግንባታ ለሀገሪቱ ንግድ መሳለጥ ከፍተኛ ፋይዳ ስላለው በፍጥነት ሊጠናቀቅ እንደሚገባ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የከተማ፣ መሠረተ ልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። የቋሚ ኮሚቴው አባላት የአዳማ-አዋሽ የፍጥነት መንገድ ግንባታ አጠቃላይ የሥራ እንቅስቃሴ ላይ የመስክ ምልከታ አካሂደዋል።   የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መሐመድ አብዱራህማን በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የአዳማ-አዋሽ የፍጥነት መንገድ ምዕራፍ አንድ ፕሮጀክት 61 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር ርዝማኔ አለው። ግንባታው በኢትዮጵያ መንግሥት እና በአፍሪካ ልማት ባንክ ድጋፍ እየተከናወነ እንደሚገኝ የጠቀሱት ዋና ዳይሬክተሩ፤ በአሁኑ ወቅት በ40 ኪሎ ሜትር በሚጠጋው የመንገድ ክፍል ላይ የሁለተኛ ዙር አስፋልት ንጣፍ ሥራ መጠናቀቁን አብራርተዋል፡፡   ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅም በአንድ ጊዜ አራት ተሽከርካሪዎችን የማስተናገድ አቅም ይኖረዋል ብለዋል። ግንባታው እንደ ወሰን ማስከበርና የካሳ ክፍያ ያሉ ተግዳሮቶች ገጥመውት የነበረ መሆኑን ጠቅሰው፤ ተቋሙ አሁን ላይ እነዚህን በማለፍ ፕሮጀክቱን ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ፕሮጀክቱን በፍጥነትና በጥራት ለማጠናቀቅ በልዩ ትኩረት እየተሠራ ይገኛል ብለዋል፡፡ የቋሚ ኮሚቴው አባላት በበኩላቸው ግንባታው ከተጀመረ ዓመታት ቢቆጠሩም በተለያዩ ምክንያቶች መዘግየቱን መታዘባቸውን ገልጸዋል። ይሁን እንጂ ችግሮችን በመቋቋም ለሀገር ኢኮኖሚ ዋልታ የሆነውን የመንገድ ፕሮጀክት ሥራን ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ለማፋጠን እየተከናወኑ ያሉ አበረታች ተግባራትን አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ አሳስበዋል።   የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መሐመድ አብዶ፤ የአዳማ-አዋሽ የፍጥነት መንገድ መጠናቀቅ የሀገሪቱን የገቢና ወጪ ንግድ ዘርፍ ለማሳደግ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። በመሆኑም አስተዳደሩ ግንባታውን በጥራትና በፍጥነት ሊያጠናቅቅ እንደሚገባ አሳስበው፤ ቋሚ ኮሚቴው ለሥራው ማነቆ የሆኑ ችግሮችን ለመፍታት የሚጠበቅበትን ግዴታ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል። የአዳማ-አዋሽ የፍጥነት መንገድ ግንባታ ፕሮጀክት የኢትዮጵያ-ጅቡቲ የትራንስፖርት ኮሪደር አካል የሆነው የአዳማ-አዋሽ-መኢሶ-ድሬዳዋ የፍጥነት መንገድ ኮሪደር ፕሮጀክት አካል መሆኑን ከተቋሙ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በክልሉ በበልግ አዝመራ የተሻለ ምርት ለማግኘት በተቀናጀ መልኩ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተከናወኑ ነው 
Jan 21, 2026 68
ቦንጋ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በበልግ አዝመራ የተሻለ ምርት ለማግኘት በተቀናጀ መልኩ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የክልሉ ግብርና ቢሮ የ2018 የበልግና የተፋሰስ ልማት ስራዎች ዕቅድ ዙሪያ በቦንጋ ከተማ የንቅናቄ መድረክ አካሄዷል።   በመድረኩ የተገኙት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)፣ ባለፉት ጊዜያት በቅንጅት በተሰሩ የግብርና ልማት ስራዎች የተገኘውን ውጤት አጠናክሮ በማስቀጠል ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። የዘንድሮውን የበልግ አዝመራ እቅድ ለማሳካትም በንቅናቄ እንደሚሰራ ገልጸው፤ መሬት ኖሯቸው ማረስ የማይችሉ ሰዎች አቅም ካላቸው ጋር ተቀናጅተው እንዲሰሩ ይደረጋል ነው ያሉት። በየደረጃው ያሉ የግብርና ባለሙያዎችም ግብዓት አጠቃቀምን ማሻሻል፣ መሬትን በተገቢው ማረስና ሌሎች ምርታማነትን ማሳደግ የሚችሉ ዘዴዎችን በተገቢው በመተግበር እቅዱን ውጤታማ ማድረግ አለባቸው ብለዋል። ለዘርፉ የተሰጠውን ትኩረትና ምቹ ሁኔታ በመጠቀም አርሶ አደሩም ራሱን ለመለወጥ መትጋት እንዳለበት አስገንዝበዋል። በሌላ በኩል የተፋሰስ ልማቱ በማህበረሰቡ ዘንድ ባህል እየሆነ መምጣቱን ያነሱት ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)፤ ዘንድሮም በተሻለ መልኩ ህብረተሰቡን በማነቃነቅ እንደሚሰራ አክለዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻዉ ከበደ በዞኑ በበልግ አዝመራ ከ98 ሺህ ሄክታር መሬት በዋና ዋና ሰብልና በሆርቲካልቸር ለማልማት የተቀናጀ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።   ለስኬቱም የግብዓት አቅርቦት፣ የእርሻ ትራክተሮች አቅርቦትና ሌሎች የቅድመ ዝግጅት ስራዎች በሰፊው በመከናወን ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው፣ በተፋሰስ ልማት ላይም ህብረተሰቡን በሰፊው በማሳተፍ ርብርብ ይደረጋል ብለዋል። የዳውሮ ዞን ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ መምሪያ የእርሻ ዘርፍ ሀላፊ አቶ ተካልኝ በቀለ የዘንድሮውን የተፋሰስና የበልግ ስራ በተለየ ትኩረት በመምራት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እንደሚሰራ ገልጸዋል።   በተለይም የቴክኖሎጂና ግብዓት አጠቃቀም ላይ የሚስተዋሉ ውስንነቶችን በማረምና ተገቢውን ድጋፍ በማድረግ ውጤታማ ስራ እንደሚሰራ ተናግረዋል።
የወጣቶችን የፈጠራ አድማስ የሚያጎለብቱ የሥልጠና ዘርፎች እየተሰጡ ነው
Jan 21, 2026 109
አዲስ አበባ፤ ጥር 13/2018(ኢዜአ)፦የወጣቶችን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትና የፈጠራ አድማስ የሚያጎለብቱ ዘመኑን የዋጁ አዳዲስ የክህሎት ማበልጸጊያ የሥልጠና ፕሮግራሞች እየተተገበሩ መሆኑን የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ወጣቶች ችሎታቸውንና ሀሳባቸውን ትርጉም ወዳላቸው ፈጠራዎች መቀየር የሚያስችል "ክህሎት ኢትዮጵያ" የተሰኘ መርሃ ግብር ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ግንቦት 14 ቀን 2015 ዓ.ም ሦስተኛውን ሀገር አቀፍ የክህሎት ውድድር ባስጀመረቡት ወቅት፤ የክህሎት ኢትዮጵያ እሳቤ ወጣቶች የማህበረሰቡን አንገብጋቢ ፍላጎቶች እንዲመረምሩና ሀገራቸውን የሚጠቅሙ መፍትሔዎችን እንዲፈጥሩ የሚያስችል ነው ማለታቸው ይታወሳል። የወጣት ፈጣሪዎችን የማምረት አቅም ለማሳደግ ድጋፍ ማድረግ እንደሚገባም አፅንኦት ሰጥተዋል፡፡ የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ብሩክ ከድር (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ የቴክኒክና ሙያ ስልጠና የመጪው ዘመን የመወዳደሪያ መድረክ ነው፡፡ የዓለም ሁኔታ ሙያና ክህሎትን የሚያበረታታ ቢሆንም በኢትዮጵያ ለክህሎት ያለን ግንዛቤ ገና አላደገም ነው ያሉት። ክህሎት የዘመናዊው ዓለም የመወዳደሪያ መስክና ጸጋ መሆኑን ገልጸው፤ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና እንደ ሁለተኛ ምርጫ መታየት የለበትም ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከለውጡ ወዲህ ያላትን የወጣቶቿን እምቅ አቅም ታሳቢ ያደረገ የቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ተግባራዊ በማድረግ ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዓለም ላይ መሪ የሆኑ የቴክኖሎጂ ውጤቶች የክህሎት ትሩፋቶች መሆናቸውን በማንሳት፤ በኢትዮጵያ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት የሥልጠናና የቅበላ አቅም እያደገ መምጣቱን አንስተዋል፡፡ የፌዴራል ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት የዘመኑ ኢንዱስትሪ የሚፈልጋቸውን ብቁና ተወዳዳሪ ባለሙያዎችን ለማፍራት ነባር የሥልጠና ዘርፎችን እያሻሻለና አዳዲሶችን ገቢራዊ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ በዚህም በ2018 ዓ.ም የሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ ሳይበር ደህንነት፣ ባዮ ሜዲካል ቴክኖሎጂ፣ ፕላስቲክ ቴክኖሎጂ፣ ሮቦቲክስ ቴክኖሎጂ እና ማንፋክቸሪንግ ቴክኖሎጂን ጨምሮ 11 አዳዲስ የሥልጠና መስኮች ተጀምረዋል ብለዋል፡፡ ኢንስቲትዩቱ ወደ ሥልጠና የሚገቡ ወጣቶችን ቁጥር ከማሳደጉም በላይ፤ አዳዲስ የሥልጠና ዘርፎችን ዘመኑን በዋጁ ቴክኖሎጂዎች አስደግፎ እየሰጠ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ይህም ከንድፈ ሀሳብ የትምህርት አሰጣጥ ይበልጥ ለተግባር ሥልጠና ያተኮረ እንዲሆን አስችሎታል ነው ያሉት። የኢትዮጵያ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ዘርፍ በመደበኛና አጫጭር ሥልጠናዎች ስድስት ሚሊዮን ዜጎችን የማስተናገድ አቅም እንዳለው ያነሱት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ሰልጣኞች ከሀገር ውስጥ ባሻገር ድንበር ተሻጋሪ አቅም እንደሚገነቡም ተናግረዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ መንግስት የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት የስልጠና ዘርፎች ሙያን በተግባር ማስተማር በሚችሉ ዘመኑ ባፈራቸው ግብዓቶች እንዲሟሉ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም ወጣቶች መሰልጠን፥ ለሥራ መዘጋጀትና ችግርን የመፍታት አቅምን ማዳበር መሆኑን ተረድተው ወደ ቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ተቋማት እንዲገቡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም