ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
ሁለገብ የገበያ ማዕከሉ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንድናገኝ አስችሎናል-ሸማቾች
May 22, 2026 34
አዲስ አበባ፤ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ሁለገብ የገበያ ማዕከሉ አምራችና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኘት ምርቶችን በብዛት፣ በጥራትና በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ማስቻሉን ሸማቾች ገለጹ። በአዲስ አበባ የተገነቡ ሁለገብ የገበያ ማዕከላት የግብይት ሰንሰለቱን በማሳጠርና የዋጋ ንረትን በመቀነስ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ይገኛሉ። ኢዜአ በለሚ ኩራ የገበያ ማዕከል ባደረገው ቅኝት ሸማቾች በማዕከላቱ ሁሉንም ዓይነት ምርቶች በማግኘት ከእንግልት መዳናቸውን ገልጸዋል። በማዕከሉ የሚገኙ የምርቶች ዋጋም ከማዕከላቱ ውጭ ከሚገኙ ገበያዎች አንጻር ሰፊ ልዩነት ያለውና ሸማቹ በተመጣጣኝ ዋጋ መግዛት የሚያስችለው መሆኑን ተናግረዋል። በለሚ ኩራ የገበያ ማዕከል ሲገበያዩ ያገኘናቸው አቶ አሊ እንድሪስ፤ የማዕከሉ መገንባት ጥራታቸውን የጠበቁ የሰብል ምርቶች፣ አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ ሌሎች ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ ማስቻሉን ገልጸዋል። ሁሉንም ዓይነት የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶች በአንድ ማዕከል ማግኘታቸው የገበያ አማራጭ እንደፈጠረላቸውም ገልጸዋል። የግብርና ምርቶችን በአቅራቢያችን በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመት የምንችልባቸው የገበያ ማዕከላት ወደ አገልግሎት መግባታቸው ተጠቃሚ እንድንሆን አስችሎናል ያሉት አቶ ባይሳ ግርማ ናቸው። በተጨማሪም የአትክልትና የፍራፍሬ ምርቶች በየቀኑ የሚገቡ ጥራት ያላቸው በመሆናቸው ለጤና ጠቃሚ መሆናቸውን ይናገራሉ። በገበያ ማዕከሉ ጤፍን ጨምሮ የተለያዩ የግብርና ምርቶች አቅማቸውን ባገናዘበ መልኩ ማግኘታቸውን ጠቅሰው ከውጭ ገበያ ጋር ሰፊ ልዩነት እንዳለው የገለጹት ደግሞ አቶ ክብሮም ገብረእግዚአብሔር ናቸው፡፡ በመዲናዋ አራቱም ማዕዘናት የተገነቡት የገበያ ማዕከላት ከደላላ ጣልቃ ገብነት ነጻ የሆኑና የግብይት ሰንሰለቱን በማሳጠር አምራቾች ምርቶቻቸውን በቀጥታ ለተጠቃሚው እንዲያቀርቡ በማስቻል ላይ ይገኛሉ። በለሚ ኩራ የገበያ ማዕከል ያነጋገርናቸው አምራች አብርሃም ንጉሴ እንዳሉትም፤ መንግስት የመስሪያ ቦታውን በነጻ በመስጠት ላደረገላቸው ትልቅ ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። በዚህም ጥራት ያላቸውን የግብርና እና የአትክልት ምርቶች ከውጪው የገበያ ዋጋ ከ15 እስከ 20 በመቶ በሚደርስ ቅናሽ ለህብረተሰቡ እያቀረቡ መሆኑን አረጋግጠዋል። ወይዘሮ መሰረት አቦባሬ እና አቶ ቶልቻ ንጉሴ በበኩላቸው፤ ምርቶቹ ያለ ምንም ጣልቃ ገብነት የሚቀርቡ በመሆናቸው የገበያ ንረትን ለመቆጣጠር ትልቅ አቅም መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህም ህብረተሰቡን በተመጣጣኝ ዋጋ በማገልገል ገበያውን ለማረጋጋት ያስቻለ በመሆኑ፣ ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ የከተማዋ ነዋሪዎችም በማዕከላቱ በደስታ እየተገበያዩ ይገኛሉ ብለዋል።  
በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መጥቷል
May 22, 2026 63
አዲስ አበባ፤ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መምጣቱን በተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) ገለጹ። በኢትዮጵያ ተግባራዊ የተደረገው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ኢትዮጵያን ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት መዳረሻ ማድረጉንም ገልጸዋል። በኢትዮጵያ እና ዱባይ መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ 6 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱም ተገልጿል።   በዱባይ የንግድ ምክር ቤት የተዘጋጀው የዱባይ - ኢትዮጵያ ቢዝነስ ትብብር ፎረም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። በተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ጀማል በከር (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የንግድና ኢንቨስትመንት የስበት ማዕከል ናት። ኢትዮጵያ በቀጣናው ለኢንቨስትመንት የተመቸ ስነ ምህዳር፣ የጂኦግራፊ አቀማመጥ ለስራ ብቁ የሆነ የሰው ሀይል ያላት ምቹ የቢዝነስ መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የወጣቶች ምድር የአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን አፍሪካውያን የገበያ መግቢያ በርና የምቹ የኢንቨስትመንት መዳረሻ መሆኗንም ገልጸዋል። የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ሁሉንም የንግድና ኢንቨስትመንት እንቅፋቶችን በማስወገድ ኢትዮጵያን ለንግድና ኢንቨስትመንት የተመቸች ሀገር አድርጓታል ብለዋል። የመስኮት የአንድ ማዕከል አገልግሎትን ጨምሮ በተሟላ መሰረተ ልማት ፈጣንና ቀልጣፋ የንግድ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ሥርዓት ተዘርግቷል ብለዋል።   ኢትዮጵያ በአፍሪካ ግዙፉ የአየር መንገድ፣ የባቡርና ተሽከርካሪ የተሳለጠ የሎጂስቲክስ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል መሰረተ ልማት መዘርጋቷን ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያና የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች መካከል ያለው ሁሉን አቀፍ ስትራቴጂያዊ ትብብር እያደገ መሆኑን ገልጸው፣ የሁለቱ ሀገራት መሪዎች በፅኑ መሰረት ላይ እንዲገነባ አድርገውታል ብለዋል። የዱባይ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዝዳንትና ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሞሐመድ አሊ ራሸድ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ወሳኝ የንግድ ኢንቨስትመንትና የገበያ መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ወሳኝ ስትራቴጂካዊ መልክዓምድር ላይ የምትገኝ በአፍሪካ ግንባር ቀደም የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ እንደምትገኝም ተናግረዋል። የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች እና ኢትዮጵያ ያላቸው የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ እያደገ መምጣቱንም ጠቅሰዋል። ሁለቱ ሀገራት በንግድ፣ ኢንቨስትመንት፣ ግብርናና መሰል መስኮች ትብብራቸው እያደገ በመምጣቱ የተባበሩት ዐረብ ኢምሬት የኢትዮጵያ ካምፓኒዎች መዳረሻ መሆኗን ገልጸዋል። በዱባይ ከአንድ ሺህ 660 በላይ የኢትዮጵያ ኩባንያዎች በንግድ፣ ሪልስቴት፣ ሎጂስቲክስና መሰል ዘርፎች ተሰማርተው እንደሚገኙ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ እና ዱባይ መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ 6 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካ ዶላር መድረሱን ገልጸው፤ የዛሬው ፎረምም የሁለቱን ሀገራት ኩባንያዎች ንግድና ኢንቨስትመንት ያጠናክራል ብለዋል።
የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ መንገድ ፕሮጀክት በይፋ ተመርቆ ለአገልግሎት በቃ
May 22, 2026 50
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ ከ672 ሚሊየን ብር በሚበልጥ ወጪ የተገነባው የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ መንገድ ፕሮጀክት በይፋ ተመርቆ ለአገልግሎት በቅቷል። በምረቃው ላይ የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፋ መሀመድ ፣ የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ ፣የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር አቶ መሀመድ አብዱራህማን ፣የክልሉ የመንገዶች ቢሮ ሀላፊ አቶ ኢድሪስ ሙሴ እና ሌሎችም ተገኝተዋል። የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፋ መሀመድ በዚህ ወቅት እንደገለጹት ተመርቆ ለአገልግሎት የበቃው የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ መንገድ ፕሮጀክት የከተማውን የንግድ ፣ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴን ለማሳለጥ ያስችላል።   መንገዱ ህብረተሰቡን ጥራት ያለው የመንገድ መሰረተ ልማት ተጠቃሚ ከማድረጉም ባሻገር የከተማውን ገፅታ በመለወጥ ረገድ የጎላ ጠቀሜታ እንደሚያበረክትም ገልጸዋል። በክልሉ ከለውጡ ወዲህ የተከናወኑ ሁለተናዊ የልማት ስራዎችን በእጥፍ በማሳደግ የህዝቡን የልማት ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማጠናከር በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ወይዘሮ ጫልቱ ሳኒ በበኩላቸው የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ የመንገድ ፕሮጀክት የጅግጅጋ ከተማን ልማትና ዕድገት በማፋጠን በኩል ያለው ጠቀሜታ ከፍ ያለ ነው ብለዋል። ሚኒስትሯ የመንገድ ፕሮጀክቱ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ድረስ ከፍተኛ አስተዋኦ ላበረከቱ ተቋማት እና ለክልሉ መንግስት ከፍተኛ ምስጋና አቅርበዋል። የኢትዮጵያ የመንገዶች አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር አቶ መሀመድ አብዱራህማን አስተዳደሩ ሀገራዊ የመንገድ መሰረተ ልማት ዕቅድን ለማሳካት እየሰራ መሆኑን ጠቁመው የጅግጅጋ ከተማ ተለዋጭ የመንገድ ፕሮጀክትም የዚሁ አካል ነው ብለዋል።   በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ተግባራዊ የተደረገው የመንገድ ፕሮጀክቱ በይርጋለም የመንገድ ኮንስትራክሽን ድርጅት አማካኝነት የተገነባ መሆኑንም ተገልጿል። የመንገድ ፕሮጀክቱ 7 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ሲሆን 30 ሜትር ስፋት ያለውም መሆኑን የክልሉ መገናኛ ብዙሃን ኤጀንሲ ዘገባ ያሳያል ።
በደቡብ ወሎ ዞን አርሶ አደሮች እያከናወኑት ያለው የግብርና ልማት ለምግብ ሉዓላዊነት እቅድ ተደማሪ አቅም የሚሆን ነው -ምክትል ጠቅላይ ሚስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 22, 2026 60
አዲስ አበባ፤ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን አርሶ አደሮች እያከናወኑት ያለው የግብርና ልማት ለምግብ ሉዓላዊነት እቅድ ተጨማሪ አቅም እንደሚፈጥር ምክትል ጠቅላይ ሚስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፣ በደቡብ ወሎ ዞን የሚገኙ አርሶ አደሮች በግብርና ልማት አብዮት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። የሃይቅ ዙሪያ አርሶ አደሮች መሬት እና እርሻቸውን ከጫት ወደ ሙዝ ክላስተር አሸጋግረው በአዲስ የልማት ግስጋሴ ላይ ናቸው ብለዋል።   አርሶ አደሮቹ የአካባቢን አንጻራዊ የልማት ጉልበት መለየት እና ወደ አትራፊ እና ዘላቂ የግብርና ጎዳና መሸጋገር ይገባል የሚለውን ሃገራዊ መርህ እና ስምሪት ተግብረው ማሳየተቻውን አመልክተዋል። በዞኑ የለጋምቦ እና የመቅደላ ወረዳ አርሶ አደሮች በስንዴ ልማት አብዮት የእርሻ ከባቢያቸውን የስንዴ ስጋጃ እያለበሱ መሆናቸውን ነው ያብራሩት። ይህ በዞኑ እየታየ ያለው የልማት ትጋት ኢትዮጵያ ለጀመረችው ለምግብ ሉዓላዊነት የጨከነ እቅድ እና ተግባር ተጨማሪ ጥሪትና ወረት እንደሆነም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው አስታውቀዋል።
በጅማ ዞን የተገነቡ መሠረተ ልማቶች ማህበራዊ ችግሮቻችንን ፈተዋል-የዞኑ ነዋሪዎች
May 22, 2026 43
ጅማ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን የተገነቡ የተለያዩ የመሠረተ ልማት አውታሮች ለጥያቄዎቻቸው ተገቢውን ምላሽ የሰጡና ማኅበራዊ ችግሮቻቸውን የፈቱ መሆናቸውን የዞኑ ነዋሪዎች ገለጹ። በዞኑ በበጀት ዓመቱ የኅብረተሰቡን ጥያቄዎች መሠረት ያደረጉ በርካታ የልማት ሥራዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት በመሆን ላይ ይገኛሉ። በዞኑ ቦቶር ጦላይ ወረዳ በዋዩ ከተማ የሚገኘው የወዴሳ ወንዝ ድልድይ ባለመሠራቱ ምክንያት ባለፉት ዓመታት ወደ ትምህርት ቤት ለመሄድ ትልቅ ፈተና እንደነበረ የገለጸችው ተማሪ ሽቶ ተፈራ ናት። አሁን ላይ ድልድዩ ተሠርቶ በመጠናቀቁ እሷም ሆነች የአካባቢው ነዋሪዎች ያለስጋት ማህበራዊም ሆነ ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮቻቸውን ለማከናወን መቻላቸውን ገልጻለች። የወረዳው ነዋሪዎች የሆኑት አቶ ደርበው ጌታቸው እና አቶ ጂሃድ ጫላ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል ወንዙን ለመሻገር በነበረው አዳጋች ሁኔታ ምክንያት ከብቶች ይወሰዱ እንደነበር አስታውሰዋል። ከዚህም ባለፈ የታመሙ ሰዎችንና ነፍሰ ጡር እናቶችን በወቅቱ ወደ ሕክምና ተቋም ማድረስ ባለመቻሉ የሰዎች ሕይወት ያልፍ እንደነበር አስታውሰው፣ የድልድዩ መገንባት ትልቅ እረፍትና ደስታ እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል። የጅማ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ዩሱፍ ሻሮ በዞኑ ባለፉት ዓመታት ለሕዝቡ የልማት ጥያቄዎች ቅድሚያ ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ 9 ድልድዮችን ጨምሮ 1 ሺህ 954 የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ተገንብተው መጠናቀቃቸውን አስታውቀዋል። ከዚህም በተጨማሪ የሕዝቡን የትራንስፖርት ችግር ለመቅረፍ የገጠር መንገድ ጥገና መደረጉን ጠቁመዋል። በበጀት ዓመቱ ከተገነቡ ፕሮጀክቶች መካከል ትምህርት ቤቶች፣ የሁለተኛ ትውልድ ጤና ኬላዎች፣ ድልድዮች እና የገጠር መንገዶች ይጠቀሳሉ ብለዋል። ፕሮጀክቶቹ በመንግሥት በጀትና በሕዝብ ተሳትፎ የተከናወኑ በመሆናቸው በቀጣይም የነዋሪውን ጥያቄ የሚመልሱ ግንባታዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል።  
መንግስት በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር እያደረገልን ባለው የተቀናጀ ድጋፍ በንብ ሃብት ልማት ውጤታማ ሆነናል
May 22, 2026 69
ዲላ፤ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፡- መንግስት በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር እያደረገልን ባለው የተቀናጀ ድጋፍ በንብ ሃብት ልማት ውጤታማ ሆነናል ሲሉ ንብ አናቢዎች ገለጹ። ዓለም አቀፍ የንብ ቀንን ምክንያት በማድረግ ሀገር አቀፍ የማር ምርትና የንብ ማነቢያ ግብዓቶች ኤግዚቢሽን በዲላ ከተማ ተካሄዷል። በወቅቱም የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ትግበራ በሀገር አቀፍ ደረጃ የንብ ሃብት እምቅ አቅምን አውጥቶ ለመጠቀም እገዛ እያደረገ መሆኑ ተመልክቷል። በተለይ ለዘርፉ የሚደረግ የግብዓት፣ የሙያና የገበያ ትስስር ድጋፍ የአልሚዎችን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ ባለፈ በርካቶች ዘርፉን እንዲቀላቀሉ በር የከፈተ መሆኑም ተገልጿል። ለዚህም ከሌማት ትሩፋት ትግበራ በፊት በዓመት 146 ሺህ ቶን ብቻ የነበረው ሀገራዊ የማር ምርት ዛሬ በ9 ወር ብቻ ከእጥፍ በላይ ጨምሮ ከ304 ቶን መሻገር ችሏል። በሀገሪቱ የተለያዩ ክልሎች የሚገኙ አልሚዎችም መንግስት በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር እያደረገላቸው ባለው የተቀናጀ ድጋፍ በንብ ሃብት ልማት ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። በጋምቤላ ክልል ማጃንግ ዞን መንገሻ ወረዳ ነዋሪው ቲቶ ሐዋርያት ለኢዜአ እንዳሉት ከሁለት ዓመት በፊት 300 ቀፎዎችን በመያዝ ወደ ንብ ማነብ ሥራ መግባታቸውን አንስተዋል። በአሁኑ ወቅት በዓመት ሶስት ጊዜ ምርት በመሰብሰብ ከ8 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ የተጣራ ማር ለገበያ በማቅረብ እስከ 700 ሺህ ብር ገቢ በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከማር ምርት ባሻገር ከሰም ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆኑን አንስተው ይሄም የሌማት ትሩፋት የተቀናጀ የመንግስት ድጋፍ ውጤት ነው ብለዋል። ለአናቢዎች የሚደረግ የግብዓት፣ የሙያና የገበያ ትስስር ድጋፎች ዘርፉን እንዲቀላቀሉ እንዳነሳሳቸው የገለፁት ደግሞ በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ላስታ ላሊበላ ወረዳ ነዋሪ ካሳዬ አየነው ናቸው።   65 ዘመናዊ ቀፎዎችን ይዘው ወደ ልማቱ መግባታቸውን አንስተው ከአንድ ቀፎ በዓመት 30 ኪሎ ግራም ማር እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። ያገኙትን ምርት ለገበያ በማቅረብ በዓመት ከ300 ሺህ ብር በላይ ገቢ በማግኘት ውጤታማ መሆናቸውን አንስተው ኤግዚቢሽኑ የገበያ አማራጭ በማስፋት ተጠቃሚነታቸውን እንደሚያጠናክር ገልጸዋል።   በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወላይታ ዞን የማንቻ የንብ ልማት ማህበር ሰብሳቢ ወጣት መሰለች በርገኒ በበኩሏ የንብ ልማት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት እንዳሸጋገራቸው ጠቅሳለች። ከሁለት ዓመት በፊት አስር ሆነው በ250 ቀፎ የጀመሩት የንብ እርባታ ከማር ምርት ባለፈ በንግስት ንብ አቅርቦት ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግራለች። በዚህም ራሳቸውን ከመቻል አልፈው ለሌሎች መትረፋቸውን ጠቅሳ ለውጤታማነታቸው የመንግስት ድጋፍ መሠረት መሆኑን ገልጻለች። በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ አቶ ደጀኔ ታከለ በበኩላቸው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ትግበራ አልሚዎችን በማነቃቃትና አዲስ በመቀላቀል የምርት ጥራትና መጠንን አሳድጓል።   ለዚህም ከሌማት ትሩፋት ትግበራ በፊት በዓመት 146 ሺህ ቶን ብቻ የነበረው ሀገራዊ የማር ምርት መጠን ዘንድሮ በ9 ወር ብቻ ከእጥፍ በላይ ጨምሮ ከ304 ቶን መሻገሩን በማሳያነት ጠቅሰዋል።    
አዲስ አበባ የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያላቸው ፕሮጀክቶች የሚገነቡባት ከተማ ሆናለች
May 22, 2026 102
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ) ፦ አዲስ አበባ የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያላቸው ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት የሚገነቡባት ከተማ እንደሆነች ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ ገለጹ። በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የቂርቆስ ክፍለ ከተማ በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ያቀዳቸውንና ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶችን አስመርቋል።   የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር ዓባይ በዚሁ ወቅት፤ በማህበረሰብ ተሳትፎ የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ዕውን ሆነዋል።   ለአብነትም በማህበራዊ ዘርፍ ባለፉት አምስት ዓመታት ለትውልድ ግንባታ መሠረት የሚጥሉ የቅድመ-አንደኛ፣ አንደኛ፣ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችና የሕፃናት ማቆያዎች መገንባታቸውን ገልጸዋል። በጤና ዘርፍም የተቋማትን አክሞ የማዳንና የበሽታ መከላከል አቅም የሚያጎለብት ውጤታማ መሠረተ ልማትና ግብዓት የማሟላት ሥራ መሰራቱን ተናግረዋል።   የአዲስ አበባ የለውጥ አብዮትም የመንገድና ስፖርት ማዘውተሪያን ጨምሮ መዲናዋን ፅዳትና ውበት ያላበሱ ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያላቸው መሠረተ ልማቶች መገንባታቸውን አንስተዋል። አዲስ አበባ የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያላቸው ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት የሚገነቡባት ከተማ መሆኗን ጠቅሰዋል። በቀጣይም የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ሰው ተኮር የልማት ሥራዎችን በመፈፀም ተወዳዳሪና ምቹ ከተማ የመፍጠር ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።   ‎የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ምስክር ነጋሽ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በክፍለ ከተማው የዜጎችን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ በርካታ ሰው ተኮር ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት መገንባታቸውን ገልጸዋል። ለአብነትም በዛሬው ዕለት የሕፃናት ማቆያዎችን ጨምሮ የቅድመ-አንደኛና የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንዲሁም ሌሎች የልማት ሥራዎች ለምርቃት መብቃታቸውን አስታውቀዋል።  
በዞኖቹ የተፈጥሮ ማዳበሪያን በስፋት በማዘጋጀት የምርት ጥራትንና የአፈር ለምነትን ለማሳደግ ጥረት እየተደረገ ነው
May 22, 2026 90
አምቦ፣ ጊምቢ፤ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ እና በምዕራብ ወለጋ ዞኖች የሰብል ምርታማነትን በዘላቂነት ለማሳደግ እና የአፈርን ለምነት ለመመለስ፣ አርሶ አደሩ የተፈጥሮ ማዳበሪያን በስፋት አዘጋጅቶ ጥቅም ላይ እንዲያውል እየተደረገ መሆኑን የየዞኖቹ ግብርና ጽሕፈት ቤቶች አስታወቁ። መንግሥት ከለውጡ ወዲህ ለግብርናው ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረት የአርሶ አደሩ የማምረት አቅም እያደገ የመጣ ሲሆን፣ አርሶ አደሩ ከፋብሪካ ማዳበሪያ በተጨማሪ በአካባቢው የሚገኙ ጸጋዎችን ተጠቅሞ የተፈጥሮ ማዳበሪያ እንዲያመርት ሰፊ ሥራ ሲሰራ መቆየቱ ይታወቃል። በምዕራብ ሸዋ ግብርና ጽሕፈት ቤት የአፈር ልማት ማሻሻያ ቡድን መሪ አቶ ተክሌ ኢዶሳ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ ከ20 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደ ሥራ ተገብቷል። አርሶ አደሮች በአካባቢያቸው ከሚገኙ ቅጠላቅጠሎች፣ ተረፈ ምርቶችና ፍግ በመጠቀም ከእቅድ በላይ 22 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ማዘጋጀት ችለዋል ብለዋል። ከዚህ በተጨማሪ ከባዮጋዝ ዝቃጭ እና ከቨርሚ ኮምፖስት ከ550 ሺህ ኩንታል በላይ ጥራት ያለው ማዳበሪያ የተዘጋጀ ሲሆን፣ ይህም በድግግሞሽ 1 ሚሊዮን ሄክታር መሬት የማልማት አቅም እንዳለው ገልጸዋል።   በተመሳሳይ በምዕራብ ወለጋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት የአፈር ለምነት ቡድን መሪ አቶ ወንድሙ ኢተፋ እንዳሉት በበጀት ዓመቱ 20 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ለማዘጋጀት ታቅዶ እስካሁን 14 ነጥብ 8 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ተዘጋጅቷል። ይህ ኮምፖስት ከ496 ሺህ 317 ሄክታር በላይ መሬት የማልማት አቅም ያለው ሲሆን፣ በአንዳንድ ወረዳዎችም ጥራቱን የጠበቀ ኮምፖስት ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የሚያደርጉ የማዘጋጃ ማዕከላት ተከፍተዋል ብለዋል። ቡድን መሪዎቹ የተፈጥሮ ማዳበሪያው የአፈርን እርጥበትና ለምነት ከመጠበቁም በላይ፣ ቀደም ሲል ምርት መስጠት አቁመው የነበሩ የእርሻ መሬቶችን ዳግም ወደ ለምነታቸው በመመለስ ምርታማነታቸውን እንዲጨምሩ አድርጓል። በተጨማሪም አርሶ አደሩ ለዘመናዊ የኬሚካል ማዳበሪያ ሊያወጣው የነበረውን ከፍተኛ ወጪ በማዳን ረገድ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ነው ያሉት። የአምቦ ወረዳ አርሶ አደር መልካሙ ባይሳ እና በሬቻ መንግሥቱ በሰጡት አስተያየት፤ ባለፉት ዓመታት በአካባቢያቸው ከሚገኙ ተረፈ ምርቶች በዓመት እስከ 38 ሜትር ኪዩብ የተፈጥሮ ማዳበሪያ እያዘጋጁ መጠቀም መጀመራቸውን ገልጸዋል። የጊምቢና አይራ ወረዳ አርሶ አደሮች ይማሙ ሌታ እና ቦካ ጅራታ በዚህም የተጎዳው አፈራቸው በማገገሙ የሰብልና ፍራፍሬ ምርታቸው በየዓመቱ እያደገ መምጣቱን አስረድተዋል።   በአሁኑ ወቅት የተዘጋጀው የተፈጥሮ ማዳበሪያ በከፊል ለበጋ መስኖና ለበልግ እርሻ የዋለ ሲሆን፣ ቀሪውን ለመኸር እርሻ ዝግጅት መሬት ላይ በመበተን ከአፈር ጋር የማዋሃድ ሥራ በስፋት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።  
ተገንብቶ ስራ የጀመረው መንገድ የረጅም ጊዜ ጥያቄያችንን የመለሰ ነው-የሰሙሮቢ ወረዳ ነዋሪዎች
May 22, 2026 113
ሰመራ፣ ግንቦት 14/2018(ኢዜአ)፡- በአፋር ክልል ተገንብቶ ለአገልግሎት የበቃው መንገድ የዘመናት የልማት ጥያቄያቸውን በአግባቡ እንደመለሰላቸው የሰሙሮቢ ወረዳ ነዋሪዎች ገለጹ። በአፋር ክልል ገቢ እና የኸሪ ራሱ ዞኖችን ለማገናኘት በ433 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የጠጠር መንገድና የድልድይ ፕሮጀክቶች የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባና የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብረሃም በላይ (ዶ/ር) በተገኙበት ተመርቆ ስራ መጀመሩ ይታወሳል። በመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስቴር የቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አማካኝነት የተገነቡት እነዚሁ ፕሮጀክቶች በክልሉ በተለያዩ ዞኖችና ወረዳዎች መካከል ያለውን የትራንስፖርት ትስስር ይበልጥ ለማጠናከርና የማህበረሰቡን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል ታስበው የተገነቡ መሆናቸውም በወቅቱ ተገልጿል። አሰተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት የሰሙሮቢ ወረዳ ነዋሪዎች ባለፉት ዓመታት በአካባቢያቸው ደረጃውን የጠበቀ መንገድ ባለመሰራቱ ምክንያት ማግኘት የሚገባቸውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞች ሳያገኙ እንዲቆዩ እንዳደረጋቸው ገልጸዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወይዘሮ ሀስና ዓሊ መንገዱ በመገንባቱ የዕለት ተዕለት ማህበራዊ ጉዳዮቻችንን በቀላሉ ለመፈጸምና ምርቶቻችንን በወቅቱ ለገበያ ለማቅረብ አስችሎናል` ብለዋል። ወጣት ኢብራሂም ቡሃዱላ በበኩሉ፤ ቀደም ሲል በነበረው የመንገድ ችግር ምክንያት ከቅርብም ሆነ ከሩቅ ዘመዶቻችን ጋር ለመገናኘትና ማህበራዊ ግዴታዎቻችንን ለመወጣት እንቸገር ነበር በማለት የነበረውን ተግዳሮት አስታውሷል። የመሰረተ ልማቱ መዘርጋት በአካባቢው ላይ አወንታዊ ተፅዕኖ ማሳረፉን የጠቀሰው ወጣቱ፤ የመንገዱ አገልግሎት መጀመር ማህበረሰባዊ ትስስርን ከመፍጠሩም ባለፈ በነዋሪዎች ህይወት ላይ ተጨባጭና መልካም ለውጥ ማምጣቱን ተናግሯል። የሰሙሮቢ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሀሰን መሐመድ በበኩላቸው፤ የተገነባው የመንገድ ፕሮጀክት የአካባቢው ማህበረሰብ ለረጅም ዘመናት በተደጋጋሚ ሲያነሳው የነበረውን የልማት እና የመሰረተ ልማት ጥያቄ በዘላቂነት መመለስ የቻለ መሆኑን አስታውቀዋል።
በክልሉ ለአምራች ኢንዱስትሪው በተሰጠ ትኩረት በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶች ቁጥር እያደገ መጥቷል - አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደ
May 21, 2026 435
ሀዋሳ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፡-በሲዳማ ክልል ለአምራች ኢንዱስትሪው በተሰጠ ትኩረት በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶች ቁጥር እያደገ መምጣቱን የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደ ገለጹ። በሀዋሳ ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የተገነባ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ ዛሬ ተመርቋል። የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ በምረቃ ሥነስርዓቱ ላይ እንዳሉት እንደ ሀገር በተፈጠረው ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በክልሉ በአምራች ዘርፉ ከፍተኛ መነቃቃት ታይቷል።   ለአምራች ኢንዱስትሪው በተሰጠው ልዩ ትኩረትም በክልሉ በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶች ቁጥር እያደገ መምጣቱ ተናግረዋል። አምራች ዘርፉ ከፍተኛ የሰው ሃይል የሚፈልግ በመሆኑ የሥራ ዕድል በመፍጠር በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም አፈ ጉባኤዋ ጠቁመዋል።   ከአነስተኛ ወደ ከፍተኛ ኢንዱስትሪ ማደግ እንደሚቻል አበባ ጨርቃ ጨርቅና ቆዳ ስፌት አክሲዮን ማህበር ያስገነባው የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካ አንድ ማሳያ ነው ብለዋል። የክልሉ አንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሀላፊ አቶ አሻግሬ ጀምበሩ በበኩላቸው መንግስት አምራች ኢንዱስትሪውን በማበረታታት በርካቶችን ወደ ሥራ እንዲገቡ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡   በክልሉ የተለያዩ ባለሀብቶች በአምራች ኢንዱስትሪው መስክ እንዲሰማሩ ለማበረታታትም በዘርፉ ለሚሰማሩ መሰረተ ልማት የተሟላላቸው ምቹ ቦታዎችን ማዘጋጀቱንም ተናግረዋል። የሀዋሳ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ሀላፊ አቶ አገና ኔቶ እንዳሉት በከተማዋ ከ1 ሺህ በላይ አነስተኛ፣ መካከለኛ እና ከፍተኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች ይገኛሉ። ኢንዱስትሪዎቹ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን የሚተኩና ለውጪ ገበያ የሚቀርቡትን በማምረት በኢኮኖሚው ውስጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆናቸውንም አስታውቀዋል። የአበባ ጨርቃ ጨርቅና ቆዳ ስፌት አክሲዮን ማህበር ሥራ አስኪያጅ ወሌ አበጋዝ (ዶ/ር) በበኩላቸው ለፋብሪካው ግንባታ ከ582 ሚሊዮን በር በላይ ወጪ መደረጉን ገልጸዋል።   በአሁኑ ወቅት ፋብሪካው ለ153 ሰዎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ እድል መፍጠሩን ገልጸው፣ በሙሉ አቅሙ ወደ ሥራ ሲገባ ለ310 ሰዎች የሥራ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ በመታገዝ ወደ ኤክስፖርት ምርት መሸጋገራቸውን ጠቁመው፣ ጥራት ያለው ምርት ለማምረትም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በትብብር እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በፋብሪካው የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ወጣት ኤደን ዘርፉ እንዳለችው በፋሽን ዲዛይን ትምህርት መስክ ተመርቃ በፋብሪካው መቀጠሯን ተናግራለች።      
በክልሉ በግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ወጣቶችን በሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ ላይ የተጀመሩ ተግባራት ይጠናከራሉ
May 21, 2026 288
ሀዋሳ፤ ግንቦት 13/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል በግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ወጣቶችን በሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ ላይ የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ገለፀ፡፡ በሲዳማ ክልል የእርሻውን ዘርፍ ለማዘመንና ሜካናይዜሽንን ለማስፋፋት በማለም የእርሻ ትራክተሮችን በዘርፉ ለተደራጁ ወጣቶች የማስረከብ መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡   በዚህ ወቅት የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ መምሩ ሞኬ እንዳሉት፤ በክልሉ እየተከናወኑ ባሉ የግብርና እና ገጠር ትራንስፎርሜሽን ሥራዎች ወጣቶችን በሥራ ዕድል ተጠቃሚ የማድረግ ተግባር እየተከናወነ ይገኛል።   የግብርና እና ገጠር ትራንፎርሜሽንን ለማረጋገጥ ግቦች ተጥለው ማሳካት የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም የምግብና ሥነ ምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ፣ ለገበያ የማምረት፣ ኤክስፖርትን የማሳደግና ገቢ ምርትን የመተካት እንዲሁም ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ የግብርና ምርቶችን በስፋት የማምረት ግቦች እንዳሉ ጠቅሰዋል፡፡ በግብርና ዘርፍ ለተደራጁ ወጣቶች የእርሻ ትራክተሮች ርክክብ መከናወኑን ገልፀው በዚህም በአጠቃላይ 148 ወጣቶች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ አስረድተዋል፡፡ የአካታችና ዘላቂ የግብርና እሴት ሰንሰለት ልማት ፕሮጀክት ብሔራዊ አስተባባሪ ሰለሞን ዳኜ በበኩላቸው ፕሮጀክቱ በገጠር በተለይ ወጣቶችና ሴቶችን አደራጅቶ ተሳታፊ በማድረግ የገጠሩን ኢኮኖሚ የማሳደግ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በመሆኑም ምርትና ምርታማነትን በማስፋትና ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በመተካት በኩል ፕሮጀክቱ የተጣለበትን ኃላፊነት ለመወጣት በትኩረት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   ትራክተሮቹን ከተረከቡ ማህበራት መካከል የቦና ወረዳ ወጣት ንግስት አምሳለ ማህበራቸው በቆሎ፣ ስንዴ እንዲሁም አቮካዶ፣ ማንጎና ሌሎች የተለያዩ ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ፍራፍሬዎችን እንደሚያመርት ገልፃለች፡፡ ከዚህ ቀደም የግብርና ሥራውን ባህላዊ በሆነ መንገድ ስለሚያከናውኑ ውጤታማነታቸው እምብዛም እንደነበር ገልፃ አሁን ላይ ሰፊ መሬትን በትራክተር በተሻለ ሁኔታ በማረስ ተጠቃሚ የሚያደርጋቸውን ዕድል እንዳገኙ ተናግራለች፡፡ የዳራ ወረዳ ወጣት አዲሱ ሌላሞ በበኩሉ ማህበራቸውም ሆነ በአካባቢያቸው ያሉ አርሶ አደሮች በበሬ አልያም በጉልበት የእርሻ ሥራቸውን እንደሚያከናውኑ ተናግሯል፡፡ ትራክተሮቹን የራሳቸውን እንዲሁም በአካባቢያቸው ያሉ አርሶ አደሮችን ማሳ ለማረስ እንደሚጠቀሙባቸው ገልጿል፡፡
የኢትዮጵያን ዕድገትና ብልፅግና በልጆቿ ጥረት ዕውን ማድረግ እንደሚቻል የገላን ኢንዱስትሪ ፓርክ ህያው ምስክር ነው
May 21, 2026 486
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ዕድገትና ብልፅግና በልጆቿ ጥረት ዕውን ማድረግ እንደሚቻል የገላን ኢንዱስትሪ ፓርክ ህያው ምስክር መሆኑን የኢንዱስትሪ ፓርኩን የጎበኙ የመዲናዋ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ግንቦት 8 ቀን 2018 የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክን መርቀው ሥራ ማስጀመራቸው ይታወቃል። ከአዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ አካባቢዎች የተውጣጡ የማህበረሰብ ክፍሎችም የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ የልማት ውጤትና የአምራቾችን የሥራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል።   በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ጽሕፈት ቤት የተጠሪ ተቋማት ዘርፍ ኃላፊ ዳዲ ወዳጆ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ የኢንዱስትሪ ክላስተር መሆኑን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኩም የአምራቾችን ዓለም አቀፍ የተወዳዳሪነት አቅም በመገንባት ሀገራዊ ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት ገንቢ ሚና እንዳለው ተናግረዋል። ለዚህም ፓርኩ የአዲስ አበባና የኢትዮጵያን የብልፅግና ጉዞ የሚያፋጥን የኢንዱስትሪ ምርታማነትን ምኅዳር እንደፈጠረ አንስተዋል። አዲስ አበባ በሁሉም ዘርፍ ስኬታማና ውጤታማ የልማት ሥራዎችን ዕውን የምታደርግ ከተማ መሆኗን የገላን ኢንዱስትሪ ፓርክ እንደሚያሳይ አስረድተዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኩም ለመካከለኛና ከፍተኛ አምራቾች ምቹ የሥራ ከባቢ በመፍጠር በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በተኪና ወጪ ንግድ የምርት አቅም መገንባት የሚያስችላቸው መሆኑን አብራርተዋል።   ከንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ የመጣው አብዱራሂም አስገዶም፤ ኢንዱስትሪ ፓርኩ ኢትዮጵያዊያን መስራትና ለውጥን ማምጣት እንደሚችሉ የሚያሳይ አስደናቂ የልማት ውጤት ነው ብሏል። የኢትዮጵያን ዕድገትና ብልፅግና በልጆቿ ጥረት ዕውን ማድረግ እንደሚቻል የገላን ኢንዱስትሪ ፓርክ ህያው ምስክር መሆኑን ተናግሯል።   ሌላኛው ከለሚኩራ የመጣው አስቻለው ሙሉጌታ በበኩሉ፤ የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ አምራቾች የሚገጥማቸውን የመስሪያ ቦታ ችግር የሚቀርፍ የልማት አቅም መሆኑን ገልጿል። የጉለሌ ክፍለ ከተማ ነዋሪዋ የጉብኝቱ ተሳታፊ ፍጹም አምሳሉ፤ የኢንዱስትሪ ፓርኩ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ለሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት አቅም የሚሆን የማምረቻ ከባቢ መሆኑን ተናግራለች።   የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ በርካታ የመዲናዋ ወጣቶችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ አስደናቂ ፕሮጀክት ነው ያለው ደግሞ ከቂርቆስ ክፍለ ከተማ የመጣው ዮኃንስ ሰለሞን ነው።   ፓርኩም የተኪ ምርታማነትን በማሳደግ ለሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ገበያ መቅረብ የሚችሉ የኢንዱስትሪ ምርቶችን የማምረት አቅም እንደሚያጎለብት ማየቱን ተናግሯል።
መንግስት ለህዝብ የገባውን ቃል ይፈፅማል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 21, 2026 419
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ መንግስት ለህዝብ የማይሰራውን ቃል አይገባም፤ ለህዝብ የገባውን ቃል ይፈፅማል ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ዛሬም የኑሮ ውድነትን ለማቃለል፣ ምርት በብዛት ማቅረቢያ እና የግብይት ማዕከላት የማስፋት ስራችን አካል የሆነው 7ኛውን የለሚ ሁለገብ የገበያ ማዕከልን ለአገልግሎት ክፍት ተደርጓል ብለዋል።   ማዕከሉ የኑሮ ውድነትን የሚያቃልሉ ዘመናዊ፣ ማሞቂያ እና ማቀዝቀዣ ያላቸው 221 መጋዘኞች፥ የችርቻሮ ሱቆች፥ ሱፐር ማርኬቶች፣ ወፍጮ ቤቶች፣ በአንድ ጊዜ 250 ተሽከርካሪዎችን ማቆም የሚችል ፓርኪንግ፣ ለለሚ ኩራ፣ ለቦሌ እና የካ ክፍለ ከተሞች ነዋሪዎች በአማካይ ቦታ እና ሰሚት ዋና መንገድ ላይ የሚገኝ ምቹ የሆነ ሁለገብ የገበያ ማዕከል ነው ብለዋል። በገበያ ማዕከሉ ማህበረሰቡ ለዕለት ፍጆታ የሚጠቀምባቸውን የሰብል ምርቶች፣ አትክልትና ፍራፍሬዎች፣ የበርበሬ ፣የቅመማቅመም ምርቶች እና የኢንዱስትሪ ምርቶችን የአንድ ማዕከል የግብይት ስርዓትን እውን ማድረግ መቻሉን ነው ከንቲባዋ የገለጹት። በማዕከሉ የሚቀርቡ ምርቶች ከ15 እስከ 20 በመቶ የዋጋ ቅናሽ የሚሸጥበት፥ ዋጋ የሚያንረውን ህገ-ወጥ የደላላ ሰንሰለት በመበጣጠስ ከአምራቹ ያልተቋረጠ ምርት የሚቀርብበትና የከተማዋ ነዋሪዎችን የኑሮ ጫና እንደሚያቃልል አመልክተዋል።   በገበያ ማዕከሉ ከተለያየ ቦታ በኮሪደር ልማት የተነሱ ነዋሪዎችን ጨምሮ ማዕከሉ ያረፈበትን 3 ነጥብ 2 ሄክታር መሬት ለልማት የለቀቁ አርሶ አደሮችም ሱቅ እንዲያገኙ መደረጉንና በዚህም ለነዋሪዎች ሰፊ የስራ እድል መፈጠሩን ተናግረዋል። ለህዝብ የገባነውን ቃል በተግባር እንዲሳካ ጥረት ላደረጉ የዲዛይንና የኮንስትሪክሽን ስራዎች ቢሮ አመራርና ሰራተኞች፣ የንግድ ቢሮ አመራሮችና ሰራተኞች፣ የለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ አመራሮች፣ ቦታው ለልማት እንዲውል ለሰጣችሁ አርሶ አደሮች በራሴና እና በከተማ አስተዳደሩ ስም አመሰግናለሁ ብለዋል።
መንግስት የአፈር ማዳበሪያን በሀገር ውስጥ ለማምረት የጀመረው ጥረት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ የልማት አቅም ነው
May 21, 2026 265
ድሬዳዋ፤ ግንቦት 13/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት የአፈር ማዳበሪያን በሀገር ውስጥ ለማምረት የጀመረው ጥረት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ የልማት አቅም መሆኑን የግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) ገልጸዋል። ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የፓናል ውይይት በድሬዳዋ ተካሂዷል።   የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት የዜጎችን ክብርና የሀገርን ሉዓላዊነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ አበረታች ስራዎች እየተሰሩ ነው። ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር በተጀመሩ ኢንሼቲቮች በሚሊየን የሚቆጠሩ ቤተሰቦችን ከልማታዊ ሴፍቲኔት በመላቀቅ ወደ አምራችነት ተሸጋግረዋል ብለዋል። እንዲሁም ከራሳቸው አልፈው ለብሔራዊ የእህል ክምችት አበርክቷቸው መጨመሩን ገልጸው እነዚህን ስራዎች በላቀ ደረጃ በማሳካት የሀገርና የዜጎችን ክብር ለመመለስ የተጀመረው የማዳበሪያ ፋብሪካ ወሳኝ እመርታ መሆኑንም አመልክተዋል።   የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ዑመር በበኩላቸው በክልሉ የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የተሰሩ ስራዎች ተጨባጭ ውጤቶች አምጥተዋል። በተለይ ከሃረማያ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ለአርሶ አደሮች የተሰጡ ድጋፎችና ክትትሎች ምርታማነትን በማሳደግ በኩል ከፍተኛ ሚና ተጫውቷል ነው ያሉት።   በሶማሌ ክልል የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን፣ ግብርናና ምግብ ዋስትና ዳይሬክተር ከድር መሐመድ በበኩላቸው ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ተከትሎ የገፀ እና ከርሰ ምድር ሃብቶችን በአግባቡ በመጠቀም አርሶ እና አርብቶ አደሮችን ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር አበረታች ስራዎች ተሰርተዋል ብለዋል። በዚህም ክልሉ ያለው ሰፊ የውሃ እና የእርሻ መሬት እንዲሁም የእንስሳት ሃብት ዜጎችን ከተረጂነት ለማላቀቅ እየዋሉ መሆኑን ገልጸዋል።   የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ልማትና ሌሎች የልማት ስራዎች አርብቶና አርሶ አደሩን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የማሸጋገሩን ጉዞ ስኬታማ ማድረጋቸውን የገለፁት ደግሞ በአፋር ክልል አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን የግብርናና ምግብ ዋስትና ከፍተኛ አስተባባሪ ከዲር ኢብራሂም ናቸው። ኢዜአ እና ግብርና ሚኒስቴር በጋራ ያዘጋጁት ሀገር አቀፍ የፓናል ውይይት በቀጣይ የተሻለ እና የተቀናጀ ስራ ለመስራት ያስችላል ብለዋል።
የመዲናዋ የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማዕከል ያደረጉ ናቸው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 21, 2026 234
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማዕከል ያደረጉ መሆናቸውን የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የተገነባውን ሰባተኛውን የለሚ ሁለገብ የገበያ ማዕከል መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።   ከንቲባዋ በዚሁ ጊዜ፤ በአዲስ አበባ የሚገነቡ ማንኛውም የልማት ሥራዎች የነዋሪዎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት የሚያስገኙ ናቸው ብለዋል። በዚህም ባለፉት አምስት ዓመታት ብቻ የመዲናዋን ነዋሪዎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ያስቻሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። የአዲስ አበባ የልማት ስኬትም ነዋሪዎችና ባለሃብቶች ባደረጉት የዕውቀት፣ የጉልበትና የገንዘብ ድጋፍና ትብብር የመጣ መሆኑንም ተናግረዋል። የለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የገበያ ማዕከልም ምርትና አገልግሎቶችን በብዛትና በጥራት በማቅረብ የገበያ መረጋጋትን የሚፈጥር ወሳኝ መሰረተ ልማት ነው ብለዋል።   ይህም የነዋሪዎችን የኑሮ ጫና በማቃለል ምርትን በብዛትና በተመጣጣኝ ዋጋ ማቅረብ እንደሚያስችል ጠቅሰዋል። ማዕከሉ ምርቶችን በቀጥታ ከእርሻ እንዲገቡ በማድረግ አላስፈላጊ የምርት ብክነትን በከፍተኛ ደረጃ መቀነስ ያስችላል ብለዋል። ማዕከሉ የጥራጥሬ፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ የቅባት እህሎችና ሌሎች መሠረታዊ የፍጆታ ዕቃዎችን በጥራት ማቅረብ የሚያስችል ዘመናዊ መሰረተ ልማት የተሟላለት መሆኑንም ተናግረዋል።
ከተረጂነት ለመውጣት በተተገበሩ ኢንሼቲቮች የራስን ችግር በራስ መፍታት እንደሚቻል ማሳየት ተችሏል
May 21, 2026 126
ድሬደዋ፤ ግንቦት 13/2018(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ከተረጂነት ለመውጣት በተተገበሩ የተሳኩ ኢንሼቲቮች የራስን ችግር በራስ አቅም መፍታት እንደሚቻል በተግባር ማሳየት መቻሉን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀውና "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" የሚል መሪ ሃሳብ ያለው የውይይት መድረክ በድሬዳዋ ከተማ ተካሂዷል።   ዶ/ር ቢቂላ ሁሪሳ በመድረኩ እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ እየተተገበረ የሚገኘው ከተረጂነት ለመውጣት ያለመው መርሃ ግብር ተጨባጭና ተስፋ ሰጪ ውጤቶችን እያስመዘገበ ይገኛል። ከሁሉም በላይ አጀንዳው በተግባር መሬት መውረዱና በአመራሩ እና በህዝቡ ዘንድ ጠንክሮ ከተሰራ ከተረጂነት መውጣት እንደሚቻል ትልቅ መነቃቃትን ፈጥሯል ብለዋል። በየደረጃው የሚገኘው አመራር በአካባቢው ያለውን የተፈጥሮ ጸጋና አቅም በመለየት፣ ህዝቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት እንቅስቃሴዎችን መጀመሩን ጠቅሰዋል። ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገው እያንዳንዱ ጥረት ከመንግስት የልማት ፕሮጀክቶች እና ዋና ዋና ኢንሼቲቮች ጋር ተናቦ መተግበሩ ለአጀንዳው ስኬታማነት ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ገልፀዋል። በየአካባቢው ከተረጂነት መውጫ የትኩረት አቅጣጫዎችን ለይቶ ስልጠና መስጠት መቻሉና የልማታዊ ሴፍቲኔት ፕሮግራምን ከአካባቢ ልማት ጋር ማስተሳሰር መቻሉ ውጤታማ አድርጎታል ነው ያሉት። ባለፉት ዓመታት በተሰሩ የተቀናጁ ስራዎች የሚከሰቱ ችግሮች በህዝብ ላይ ሊያደርሱ የሚችሉትን ስጋቶች መቀነስ ተችሏል ያሉት ሚኒስትሩ፤ ይህም በበርካታ ተጋላጭ ወረዳዎች ላይ በተግባር መረጋገጡን አንስተዋል። በዚህም መሠረት በርካታ ዜጎች ከተረጂነት ወጥተው፣ ትርፍ አምራች በመሆን ሀብት ማፍራት የጀመሩ ሲሆን፤ ከራሳቸው ፍጆታ አልፈው ለሌሎች መትረፍ የቻሉበት ደረጃ ላይ መደረሱን አብራርተዋል። ከእንስሳት ሀብት ልማት አንጻርም በተሻለ ሁኔታ ውጤታማ የሆኑ በርካታ የአርብቶ አደር አካባቢዎች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ ለሌሎች አካባቢዎች የእንስሳት መኖ ማቅረብ የጀመሩ መኖራቸውን በአብነት አንስተዋል። በአጠቃላይ በመርሃ ግብሩ የተከናወኑ ስራዎች ኢትዮጵያ የራስን ችግር በራስ የመፍታት አቅም እንዳላት በተግባር ያረጋገጠችበት ታሪካዊ ጉዞ መሆኑን ሚኒስትሩ አስረድተዋል። በመርሃ ግብሩ አማካኝነት በገጠር አካባቢዎች የመሰረተ ልማት ተደራሽነትን በሰፊው ማስፋፋት መቻሉ፣ በተለይም የሴቶች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እንዲያድግ ተደርጓል ብለዋል። በዚህም ህብረተሰቡ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን የመቋቋም አቅሙ ጎልብቷል ነው ያሉት። በተሰሩ ስራዎች አደጋዎችን መቋቋም ተጀምሯል፤ ኢትዮጵያም የራሷን ችግር በራሷ መፍታት እንደምትችል ለዓለም ማሳየት ጀምራለች ሲሉ ተናግረዋል።
በክልሉ የመንግስት ሰራተኛው ፈጣንና ፍትሃዊ አገልግሎት በመስጠት የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ ይሰራል
May 21, 2026 101
ባህርዳር፤ ግንቦት 13/2018(ኢዜአ)፦ የመንግስት ሰራተኛው ፈጣንና ፍትሃዊ አገልግሎት በመስጠት የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ የድርሻውን መወጣቱን እንደሚቀጥል የአማራ ክልል ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ባንችአምላክ ገብረማርያም ገለጹ። ‎‎የመንግስት ሰራተኛውን በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የሚያወያይ መድረክ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው።   የቢሮ ኃላፊዋ በወቅቱ እንደገለፁት፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉና ለሀገር እድገት ዘላቂ መሰረት የጣሉ የልማት ፕሮጀክቶች መተግበራቸውን ገልፀዋል። በየደረጃው እየተመዘገበ ላለው ውጤት የመንግስት ሰራተኛው ፈጣንና ፍትሐዊ አገልግሎት በመስጠት የልማት ስራዎች በመደገፍ የድርሻውን መወጣቱን መቀጠል ይገባዋል ነው ያሉት። ኮሪደርን መሰረት ያደረገው የከተሞች ልማት፣ መሶብ የአንድ ማእከል አገልግሎት፣ የአረንጓዴ አሻራ፣ የበጋ ስንዴና ሌሎች ኢንሼቲቮች በክልሉ ውጤት ከተመዘገበባቸው መስኮች መካከል ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። ‎በትምህርትና በጤናው ዘርፎችም ይታዩ የነበሩ ችግሮችን ለማቃለል በተከናወኑ ተግባራት ጤናማ፣ ብቁና ሀገር ወዳድ ዜጋ ማፍራት እየተቻለ እንደሚገኝ አስገንዝበዋል። የተጀመሩ የልማት ተግባራትን አጠናክሮ ለማስቀጠል የመንግስት ሰራተኛው የድርሻውን መወጣት ይጠበቅበታል ሲሉ አስገንዝበዋል።   ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል አቶ ስንታየሁ ስንሻው እና አቶ ላመስግን አዳነ እንደገለጹት፤ የክልሉን የሀገር ልማትና ዕድገት በማፋጠን የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ኃላፊነታቸውን በመወጣት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል።   በተለይም ፈጣን፣ ቀልጣፋና ፍትሐዊ አገልግሎት መስጠት ላይ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ነው የገለጹት።
በከተማዋ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ማደግ ሰፊ የሥራ ዕድል ፈጥሮልናል -የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪዎች
May 21, 2026 146
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦የወላይታ ሶዶ ከተማ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ማደግ ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ በከተማዋ በተለያየ ዘርፍ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ነዋሪዎች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በወላይታ ሶዶ ከተማ ያለው የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ እያደገ በመምጣቱ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ አድርጓቸዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወጣት ገዛኸኝ ገብሬ እና አቶ አበራ አርካ፤ በኢንዱስትሪ ዘርፍ በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል የተሻለ ገቢ እያገኙና ኑሯቸውም እየተሻሻለ መምጣቱን ተናግረዋል። ከዚህ ቀደም በአነስተኛ ገቢ ይተዳደሩ እንደነበር አስታውሰው፣ በከተማው እየተነቃቃ የመጣው የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ለነዋሪዎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ተጨማሪ አቅም መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም በተፈጠረላቸው የሥራ ዕድል ከሚያገኙት ገቢ በመቆጠብ የራሳቸውን ሥራ የመፍጠር ዕቅድ እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ በሪል ስቴት የግንባታ ዘርፍ የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ዙፋን ሰይድ፣ ሚናሴ ዲዲምስ እና ኤልሳዬ ምልኪያስ በበኩላቸው እንዳሉት፤ ቀደም ሲል የነበረው የሥራ ዕድል ጠባብ በመሆኑ ጊዜያቸውን በአልባሌ ቦታ ያሳልፉ ነበር። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በከተማዋ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን ተከትሎ የተጀመሩ የግንባታ ፕሮጀክቶች የአካባቢያቸውን ገጽታ የሚቀይሩ ከመሆን ባለፈ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ተናግረዋል። እነሱም ባገኙት የሥራ ዕድል ተጠቅመው ቤተሰቦቻቸውን ጭምር እያገዙ መሆናቸውን ገልጸው፣ ለአካባቢው ልማት ቀጣይነት የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁነታቸውን አረጋግጠዋል። ከተማ አስተዳደሩ ባደረገላቸው ድጋፍ በ40 ሚሊዮን ብር ካፒታል ወደሥራ እንደገቡ የተናገሩት ደግሞ የራማ ፋሚሊ ፒቪሲ፣ ኤች ዲፒ እና ፕላስቲክ ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሳዲቅ አብዱልሃዲ ናቸው፡፡   በአሁን ወቅት ካፒታላቸው ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ መድረሱን ጠቅሰው ከ40 ለሚበልጡ ዜጎችም ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል፡፡ የኢያሱ ያዕቆብ ኮንስትራክሽን ሥራ አስኪያጅና ባለቤት ኢንጂነር ኢያሱ ያዕቆብ በበኩላቸው፣ የከተማ አስተዳደሩ ለሪል ስቴት ግንባታ ያቀረቡትን ጥያቄ በአጭር ጊዜ ውስጥ በማጽደቁ በ500 ሚሊዮን ብር ካፒታል የመጀመሪያ ዙር የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል።   በዚህም ከ370 በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው ወጣቶች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል። ድርጅታቸው በከተማው የሚስተዋለውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል ከከተማ አስተዳደሩ ጋር በቅንጀት እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ 29 የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ወደሥራ መግባታቸውን የገለጹት ደግሞ የወላይታ ሶዶ ከተማ ኢንቨስትመንት ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቸርነት ተስፋዬ ናቸው።   ኢንቨስትመንቶቹ በአገልግሎት፣ በኢንዱስትሪ፣ በግንባታና ሌሎች ዘርፎች ላይ ያተኮሩ እንደሆነም አመልክተዋል። በዚህም ከ1 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል ያሉት ኃላፊው፣ ወጣቶችም የቴክኖሎጂ እና የክህሎች አቅማቸውን ለማሳደግ ተጨማሪ ዕድል አግኝተዋል ብለዋል።
በምግብ ራሱን የቻለ ትውልድ የመገንባት ጥረት የሀገርን ክብርና ሉአላዊነት እውን የማድረግ ቁልፍ አጀንዳ ነው 
May 21, 2026 159
ድሬዳዋ ፤ ግንቦት 13/2018 (ኢዜአ)፦ ከተረጅነት በመውጣት በምግብ ራሱን የቻለ ትውልድ የመገንባት ጥረት የሀገርን ክብርና ሉአላዊነት እውን የማድረግ ቁልፍ አጀንዳ መሆኑን በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር "ከተረጂነት ወደ ምርታማነት" በሚል መሪ ሃሳብ የተዘጋጀው የውይይት መድረክ በድሬዳዋ ተካሄዷል።   በመድረኩ ላይ የውይይት መነሻ ሐሳብ ያቀረቡት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)፤ ከተረጅነት የመውጣትን ጉዳይ መንግስት ወሳኝ ሀገራዊ አጀንዳ አድርጎ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በምግብ ራሱን የቻለ ትውልድ የመገንባት ጥረት የሀገርን ክብርና ሉአላዊነት እውን የማድረግ ቁልፍ አጀንዳ መሆኑን አንስተው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በትውልድ ቅብብሎሽ የመጣውን በእርዳታ የመኖር የጥገኝነት አመለካከት አከርካሪ በመስበር የሀገርን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ የተጀመረውን አበረታች ጉዞ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር፣ ሂደቱን በሁለንተናዊና በተሟላ አስተሳሰብ መምራት ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ በቂና የተሟላ የውሃ ሀብት፣ የተማረና አምራች የሆነ ወጣት የሰው ኃይል እንዲሁም ለም የመሬት ፀጋዎች ያሉባት ሀገር በመሆኗ በማልማት እድገትና ማንሰራራትን ማስቀጠል ይቻላል ሲሉ ተናግረዋል። ከተረጂነት ለመላቀቅ የሚያግዙ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እሴቶችን በመጠቀም፣ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በፍጥነትና በፈጠራ የተመሩ የግብርና ልማት ስራዎች በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ ተጨባጭና እመርታዊ ለውጥ እያመጡ ነው ብለዋል። በምግብ ራስን የመቻል ራዕይ ከቤተሰብ ኑሮ ለውጥ እንደሚጀምር ጠቅሰው፤ ዜጎች በሰፊው አምራች እንዲሆኑ፣ የተመረተውን በአግባቡ በመጠቀምና በመቆጠብ መጠቀም እንዲችሉ እንዲሁም ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገር እንዲችሉ መደገፍ አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። ዋናው መሠረታዊ ጉዳይም ያሉንን አቅሞች በመለየትና ህዝብን ወደ ላቀ ምርታማነት ደረጃ በማሸጋገር በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ አስተሳሰብና አተገባበር በላቀ ደረጃ ማስቀጠል መቻል መሆኑን አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም