ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የሕዳሴ ግድብ ለቀጣናው ሀገራት የኃይል አቅርቦትን ከማረጋገጥ ባለፈ በትብብር ላይ የተመሠረተ ግንኙነትን ለማጠናከር ያግዛል
Jun 5, 2026 353
አሶሳ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለቀጣናው ሀገራት የኃይል አቅርቦትን ከማረጋገጥ ባለፈ በትብብር ላይ የተመሠረተ ግንኙነትን ለማጠናከር እንደሚያግዝ ተመላከተ። የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ቀጣናዊ ትብብርን በማሳለጥ እና የአባይ ተፋሰስን በዘላቂነት ማልማት ላይ ያተኮረ 4ኛው አለም አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስ አካሂዷል።   በወቅቱም በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ዘሪሁን አበበ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሁፍ እንደገለፁት፤ ሕዳሴ ግድብ ለቀጣናው ሀገራት የኃይል አቅርቦትን ከማረጋገጥ ባለፈ በትብብር ላይ የተመሠረተ ግንኙነትን ለማጠናከር ያግዛል። ኢትዮጵያ በአባይ ወንዝ ላይ ያላትን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተከናወኑ የሚገኙ የምርምር ስራዎችን በማጠናከር ሀሰተኛ ክሶችንና መረጃዎችን መመከትና እውነቱን ማስረዳት ከምሁራን ይጠበቃል ብለዋል። የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ለግድቡ ቅርብ ከመሆኑ የተነሳ መሰል የጥናትና ምርምር ስራዎችን በማጠናከር የሕዳሴ ግድብ ከኢትዮጵያ ባለፈ ለቀጣናው ሀገራት የሚያስገኘውን ፋይዳ ማሳወቅ እንደሚገባው አመልክተዋል።   የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ያሬድ ሙሉ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በግድቡ አካባቢው የሚኖረው ማህበረሰብ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በኮንፈረንሱ ላይ የአፍሪካና የአውሮፓ ሀገራት የዘርፉ ተመራማሪዎች በበይነ መረብ ጥናታቸውን ያቀረቡ ሲሆን በግድቡ እና በአባይ ተፋሰስ ልማት ዙሪያ ዓለም አቀፍ ተሞክሮዎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
በክልሉ የግብርና ቴክኖሎጂን በስፋት በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 5, 2026 230
መቱ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል የእርሻ መሬትን ከማስፋፋት ባለፈ የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማጎልበት ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱ ተገለጸ። በኢሉአባቦር ዞን የመኸር አዝመራ በተጠናከረ መልኩ የቀጠለ ሲሆን በዛሬው ዕለት በዶረኒ ወረዳ የተዘጋጀ መሬት በበቆሎ ዘር የመሸፈን ስራ ተጀምሯል።   በዚሁ ጊዜ የኦሮሚያ ክልል መስኖና አርብቶ አደር ልማት ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር ግርማ ረጋሳ፤ በክልሉ የበጋና ክረምት እርሻ ስራ በስፋት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በተለይም በክልሉ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በመስኖ ልማት ስራ ትልቅ ውጤት መገኘቱን ጠቅሰው የአነስተኛ እና መለስተኛ መስኖ ልማት ግድቦች ግንባታ መጠናከሩንም ገልጸዋል። የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚቻለው በዋናነት ግብርናን በማስፋፋት መሆኑን የገለጹት ኢንጂነር ግርማ፣ በበጋ ስንዴ ልማት በክልሉ ትልቅ ስኬት መመዝገቡን አስታውሰዋል። ይህም ቀድሞ የነበረውን በዓመት አንዴ የማምረት ባህል በማሻሻል፣ ለክረምት እርሻው ተጨማሪ ትልቅ አቅም መፍጠሩን ገልጸዋል። በተያዘው የመኸር አዝመራም ለግብርና ልማት መዋል የሚችለውን መሬት አሟጦ በማረስ እና የግብርና ሜካናይዜሽንን በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል ብለዋል።   በኢሉአባቦር ዞን በክረምት እርሻ 389 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ለመሸፈን እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ ናቸው። በዞኑ ወረዳዎች የኩታ ገጠም እርሻዎችን በዘር የመሸፈን ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉንም አንስተዋል። በሁሉም ወረዳዎች ምርታማነትን የሚያሳድግ የግብርና ሜካናይዜሽን አቅርቦት እያደገ መምጣቱን የጠቀሱት ዋና አስተዳዳሪው፣ የክረምት እርሻው በትራክተር በመታገዝ እንዲታረስ ትኩረት መሰጠቱን አክለዋል።   የዶረኒ ወረዳ ግብርና ልማትና መሬት አስተዳደር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ ለሊሴ አመና በበኩላቸው፣ በወረዳው በክረምት እርሻ ከ17 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች የማልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። በዚህም በተለይ የበቆሎ ምርትን በእጥፍ ለማሳደግ መታቀዱን ገልጸዋል። በክረምት እርሻው ላይ የተሰማሩ የወረዳው አርሶ አደሮችም፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከሚረዱ ሰብሎች ጎን ለጎን ከፍተኛ የኢኮኖሚ ጠቀሜታ ያላቸውን ሰብሎችም በትኩረት እንደሚያመርቱ ተናግረዋል።  
በሲዳማ ክልል የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ ለሪፎርም ሥራዎች ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 5, 2026 247
ሀዋሳ፣ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ)፡-የመንግስት አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን የተገልጋይ እርካታን ለማሳደግ ለሪፎርም ሥራዎች ትኩረት መስጠቱን የሲዳማ ክልል ገንዘብ ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ዓላማ ላይ ለባለድርሻ አካላት ያዘጋጀው የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ በሃዋሳ ከተማ ተካሂዷል።   የቢሮው ሀላፊ አቶ ሀይሌ ሀርሲሳ ለኢዜአ እንደገለጹት በቢሮው የመንግስት አገልግሎትን ቀልጣፋ፣ ተደራሽና ፍትሀዊ ለማድረግ የአስተዳደር ሪፎርም ተግባራዊ ማድረግ አስፈላጊ ነው። የሪፎርም ሥራው የበጀት ሥራዎችን በቴክኖሎጂ ተደግፎ ለማከናወን ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንም አንስተዋል። ቢሮው የክፍያ ስርዓቱ በኤሌክትሮኒክስ የሚከናወንበትን አሰራር በመዘርጋት አገልግሎቱን ከጥሬ ገንዝብ ንክኪ ነጻ በማድረግ ግልጸኝነትና ተጠያቂነት የማስፈን ሥራ መጀመሩንም ተናግረዋል።   በሲዳማ ክልል ገንዘብ ቢሮ የሪፎርም ቴክኒክ ቡድን አስተባባሪ አቶ ጌቱ በቀለ በበኩላቸው እንዳሉት በቢሮው ቀደም ሲል ይሰጡ የነበሩ አገልግሎቶች በሪፎርሙ ደረጃ ወጥቶላቸው እየተከናወኑ ይገኛሉ። ሪፎርሙ የተቋሙን አሰራር እና የሠራተኛውን የመፈጸም አቅም በማሳደግ የህዝብ ተቀባይነትና አመኔታን ለመፍጠር የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ በገንዘብ ሚኒስቴር የሪፎርም ድጋፍ ቡድን ሀላፊ አቶ ይገዙ ዳባ ናቸው።   ተግባራዊ የሚደረገው የመንግስት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ለዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል ብለዋል።
በፓርኩ ለአቮካዶ ዘይት አምራች ኢንዱስትሪዎች ምርት የሚያቀርቡ ማህበራት ተጠቃሚ ሆነዋል
Jun 5, 2026 356
ሀዋሳ ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦በይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ማቀነባበሪያ ፓርክ ከአምራች ኢንዲስትሪዎች ጋር በተፈጠረላቸው የገበያ ትስስር ተጠቃሚ መሆናቸውን በአቮካዶ ምርት ማቅረብ ሥራ ላይ የተሰማሩ የአርሶ አደር ማህበራት ገለጹ። በይርጋለም ኢንዱስትሪ ፓርክ ከሚንቀሳቀሱ 10 አምራች ኢንዱስትሪዎች አራቱ በአቮካዶ ዘይት ማምረት ሥራ ላይ የተሰማሩ ሲሆን ይህም ለአካባቢው አርሶ አደሮች የገበያ ትስስር በመፍጠር ተጠቃሚ እያደረጋቸው ነው። በተለይም አርሶ አደሩ በሕብረት ሥራ ማህበራት ተደራጅቶ ምርቱን ለኢንዱስትሪዎች እንዲያቀርብ ምቹ ዕድል እየፈጠረ መጥቷል፡፡ አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ማህበራት መካከል የ"ዶንጎራ ቀዋዶ አትክልትና ፍራፍሬ አምራችና አቅራቢ ማህበር" ሰብሳቢ አቶ ላታሞ ያዕቆብ እንደገለጹት፤ ማህበሩ በአምስት መሰረታዊ የሕብረት ሥራ ማህበራት በርካታ አርሶ አደሮችን አቅፎ የአቮካዶ ምርትን ለኢንዱስትሪዎች እያቀረበ ይገኛል።   ይህም ቀደም ሲል አርሶ አደሩ ገበያን በማፈላለግ ያጋጥመው የነበረውን የምርት፣ የጊዜና የጉልበት ብክነት በማስቀረት የተሻለ ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻሉን ተናግረዋል። የማህበሩ አባላት የአቮካዶ ምርታቸውን በማህበሩ በኩል በቀጥታ ለኢንዱስትሪዎች በማቅረብ ገቢያቸውን እያሳደጉ መሆኑንም ገልጸዋል። ሌላው የ”ፋያ ኢንተርፕራይዝ ማህበር” ሰብሳቢ ወጣት ሻላ ካሳ፤ በማህበር ተደራጅተው የአቮካዶ ምርትን በፓርኩ ውስጥ ለሚገኙ ኢንዱስትሪዎች በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን ገልጿል።   በቀን ከ50 ሺህ እስከ 80 ሺህ ኪሎ ግራም የአቮካዶ ምርት ሰብስበው እንደሚያቀርቡ ገልጾ፣ በምርት አሰባሰብ ሂደት ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል ብሏል። አሁን ላይ ገቢና ተጠቃሚነታቸው በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንም ተናግሯል። የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሀይሉ የተራ በበኩላቸው እንዳሉት፤ በአሁኑ ወቅት በፓርኩ በአቮካዶ ዘይት ለተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች ተደራጅተው ምርት የሚያቀርቡ አርሶ አደሮች ተጠቃሚ እየሆኑ ነው።   ፓርኩ ወደሥራ ከገባ ያለፉት አምስት ዓመታት ከ83ሺህ ቶን በላይ የአቮካዶ ምርት ለፓርኩ መቅረቡን የጠቆሙት አቶ ሀይሉ፣ ለበርካቶች የሥራ ዕድል ለመፍጠር መቻሉንም ተናግረዋል። በማህበር ተደራጅተው ለኢንዱስትሪዎቹ የአቮካዶ ምርት የሚያቀርቡ አርሶ አደሮችም ተጠቃሚ እየሆኑ ይገኛሉ ብለዋል። አቶ ሀይሉ እንዳሉት በ43 ማህበራት የተደራጁ ከ132ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ምርታቸውን ለፓርኩ በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ ይገኛሉ፡፡
በኦሮሚያ ክልል በዚህ ዓመት 16 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል ቡና ተመርቷል
Jun 5, 2026 156
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦ በኦሮሚያ ክልል በተጠናቀቀው የምርት ዘመን 16 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል አጠቃላይ የቡና ምርት መገኘቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የቡና ጥራት እና ልማት ዳይሬክተር አቶ ታከለ ኃይለማርያም ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በክልሉ የቡና ልማት በልዩ ኢንሼቲቭ ተቀርጾ ወደ ስራ ከገባ ወዲህ፣ የቡና ምርትና ምርታማነት በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መጥቷል። የአርሶ አደሩ ህይወትና ኑሮ ከቡና ልማት ጋር በቀጥታ የተሳሰረ መሆኑን የጠቀሱት ዳይሬክተሩ፤ የቡና ልማቱ በስፋትና በዘመናዊ መልኩ መከናወኑ የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደገ መሆኑን ገልጸዋል። ቢሮው የቡና ምርትን በዓይነትና በብዛት ለማሳደግ በርካታ ስራዎችን ተግባራዊ ማድረጉን ጠቁመዋል። ከእነዚህም መካከል በአጭር ጊዜ ውስጥ ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን ለአርሶ አደሩ ማድረስ፣ ያረጁና ምርት የማይሰጡ የቡና ተክሎችን በአዲስ የመተካት ዋና ዋናዎቹ ናቸው ብለዋል። በተጨማሪም በግብርና ባለሙያዎች በመታገዝ የቡና ተክሎችን የመጎንደል ስራን በስፋት ማከናወን መቻሉንም ገልጸዋል። በዚህም በክልሉ በ2018 የምርት ዘመን 18 ሚሊዮን ኩንታል የቡና ምርትን ለመሰብሰብ ታቅዶ፣ በእስካሁኑ ሂደት 16 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ማግኘት ተችሏል ብለዋል። ቡና በዓለም ገበያ ያለውን ተወዳዳሪነትና ጥራት ለማስጠበቅ አርሶ አደሩን ማዕከል ያደረጉ ተከታታይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች መሰራታቸውን አቶ ታከለ አብራርተዋል። በተለይም አርሶ አደሮች የደረሰ ቀይ ቡና ብቻ እንዲለቅሙ ማድረግ የተቻለ መሆኑን የገለጹ ሲሆን የተሰበሰበውን ቡና በጥራት የማድረቅ ባህል ማደጉን ተናግረዋል። የአርሶ አደሩን የምርት ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማሳደግና ህገ-ወጥ ደላሎችን ለመከላከል፣ ምርቱን ያለማንም ጣልቃ ገብነት በቀጥታ ወደ ማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታዎች እየተፈጠሩ መሆናቸውን ኃላፊው አስታውቀዋል።
በዞኑ በሚገኙ ከተሞች እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የነዋሪውን ተጠቃሚነት እያሳደገ ነው
Jun 5, 2026 136
ደሴ ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦በደቡብ ወሎ ዞን በሰባት ከተማ አስተዳደሮች እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የነዋሪውን የልማት ተጠቃሚነት እያሳደገ መምጣቱን የዞኑ ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የመሰረተ ልማት ቡድን የኮንስትራክሽን አስተዳደር መሃንዲስ አደም መሃመድ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በዞኑ የሕብረተሰቡን የመሰረተ ልማት ጥያቄ ደረጃ በደረጃ ለመመለስ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ ነው። በተለይ ከተሞችን በኮሪደር ልማት በማስዋብና በማሳመር ለነዋሪዎች፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ የማድረግ ስራ እየተከናወነ ይገኛል ነው ያሉት። በዚህም በሐይቅ፣ ሀርቡ፣ ጊምባ፣ ወረኢሉ፣ መካነሰላም፣ አቀስታ እና ደጎሎ ከተማ አስተዳደሮች የኮሪደር ልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። እስካሁን በተደረገ የተቀናጀ ጥረት በተወሰኑ ከተሞች የኮሪደር ልማቱን አጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ማድረግ እንደተቻለ ገልፀዋል። ቀሪውንም የልማት ስራ እስከ በጀት ዓመቱ መጨረሻ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ለማብቃት ሰፊ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። የኮሪደር ልማቱ የብስክሌትና የእግረኛ መንገድን ጨምሮ መዝናኛና ሌሎችንም ያካተተ በመሆኑ ከተሞችን በማነቃቃት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ እንዳስቻለም አብራርተዋል። ለኮሪደር ልማት ስራው ከ527 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ተይዞለት እየተከናወነ ሲሆን ህብረተሰቡ ገንዘብ በማዋጣት፣ በጉልበቱና የግንባታ ቁሳቁስ በማቅረብ ከፍተኛ እገዛ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የሐይቅ ከተማ ነዋሪ አቶ እንድሪስ ሰይድ በሰጡት አስተያየት፣ የከተማው የኮሪደር ልማት ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉ ለነዋሪዎች ምቹ ከመሆኑ ባለፈ ከተማው እንዲነቃቃ አድርጓል። በፍጥነት የተጠናቀቀው ኮሪደሩ የብስክሌትና የእግረኛ መንገድን ጨምሮ ሌሎችንም መዝናኛዎች ያካተተ በመሆኑ የተሽከርካሪ አደጋንም መቀነስ አስችሏል ብለዋል። የዚሁ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ እናትነሽ በሽር በበኩላቸው፣ ''የከተማው የኮሪደር ልማት በፍጥነት ተጠናቆ አገልግሎት እንዲጀምር እኛም በገንዘብ፣ በጉልበትና በሀሳብ የድርሻችንን ተወጥተናል'' ብለዋል። ልማቱ የከተማውን ውበት ከማሳመር ባለፈ ከተማው የቱሪዝም መዳረሻ እንዲሆንም እያገዘ እንደሆነ አንስተዋል። ''ከተማችን በኮሪደር ልማት እየተዋበችና እየደመቀች በመሆኑ ተደስተናል'' ያሉት ደግሞ የሀርቡ ከተማ ነዋሪ አቶ አሊ አህመድ ናቸው።
በግብርናው ዘርፍ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎች ይጠናከራሉ
Jun 5, 2026 149
ዱራሜ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በግብርና ዘርፍ ያሉ ፀጋዎችን ለልማት በማዋል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎች እንደሚጠናከሩ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው ከተለያዩ ዞኖች እና ከጠምባሮ ልዩ ወረዳ ለተውጣጡ የልማት ጣቢያ ሠራተኞች ያዘጋጀው የግንዛቤ ማጎልበቻ ስልጠና በዱራሜ ከተማ እየተሰጠ ነው።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ በግብርናው ዘርፍ ያሉ ፀጋዎችን ወደልማት በመቀየር ከዘርፉ አርሶ አደሩን ተጠቃሚ ለማድረግ የተጀመሩ ሥራዎች ይጠናከራሉ። ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የቴክኖሎጂ ሽግግር ወሳኝ እንደሆነ ያነሱት አቶ ኡስማን፣ ለዚህ ስኬትም የግብርና ልማት ጣቢያ ሠራተኞች ሚና ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል። የአካባቢውን ፀጋ ለይቶ በማልማት ረገድ በተሰራው ሥራ በርካታ አርሶ አደሮች ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ገልጸው፣ በዚህም አርሶ አደሮች ከራሳቸው ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ሆነዋል ብለዋል። በተጨማሪም የኢንዱስትሪና የወጪ ምርቶችን በማምረት ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ነው የገለጹት። በዘርፉ እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶችን ወጥነት ባለው መልኩ ለማጠናከር ለግብርና ልማት ጣቢያ ሠራተኞች የዛሬው የአቅም ግንባታ ስልጠና መዘጋጀቱን ተናግረዋል። ሠራተኞቹ ግብርናን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመረውን ጥረት አጠናክረው ማስቀጠል እንዳለባቸውም አቶ ኡስማን አሳስበዋል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ አቡቶ አኒቶ በበኩላቸው እንዳሉት፤ አርሶ አደሩን በቅርበት በመደገፍ ምርትና ምርታማነቱ እንዲጨምር በማድረግ በኩል የግብርና ልማት ጣቢያ ሠራተኞች ሚና የጎላ ነው። ቴክኖሎጂን ለአርሶ አደሩ በማሸጋገር፣ ግብርናን በማዘመንና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ የሚጠበቅባቸውን ሚና ማጠናከር እንዳለባቸውም አፈ ጉባኤው አሳስበዋል። በመድረኩ ከከምባታ እና ከሀድያ ዞኖች እንዲሁም ከጠምባሮ ልዩ ወረዳ የተውጣጡ ከ1ሺህ 700 በላይ የልማት ጣቢያ ሠራተኞች እና የተለያዩ የሥራ ሀላፊዎች በመሳተፍ ላይ ናቸው።
የሆሳዕና ከተማ ነዋሪዎች በጠቅላላ ምርጫው ያሳዩትን ንቁ ተሳትፎ በሁሉም የልማት መስኮች ለመድገም ተዘጋጅተዋል
Jun 5, 2026 102
ሆሳዕና፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦የሆሳዕና ከተማ ነዋሪዎች በጠቅላላ ምርጫው ያሳዩትን ንቁ ተሳትፎ በቀጣይ በሁሉም የልማት ሥራዎች ላይ በድጋሚ ለማረጋገጥ መዘጋጀታቸውን ገለጹ። በሆሳዕና ከተማ የሴች ዱና ቀበሌ ነዋሪዋ ወይዘሮ እንዳሻሽ ፀጋዬ እንደገለጹት፤ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በመሳተፍ ይበጀናል ለሚሉት ፓርቲ ድምፅ ሰጥተዋል። በምርጫ ወቅት ያሳዩትን ንቁ ተሳትፎ በቀጣይም በሀገር ልማት ላይ በመድገም የተጀመረውን ሀገራዊ ልማት ለማስቀጠል ዝግጁ መሆናቸውንም አረጋግጠዋል። በከተማው በሊች አምባ ቀበሌ የሚኖሩት አቶ ሀብቴ አስራት በሰጡት አስተያየት፤ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በመሳተፍ ይበጀኛል ላሉት የፖለቲካ ፓርቲ ድምጻቸውን ሰጥተዋል። በምርጫው ያሳዩትን ንቁ ተሳትፎ በቀጣይም በልማት እንደሚደግሙት ገልፀዋል። በሆሳዕና ከተማ ሄጦ ቀበሌ ነዋሪዋ ዓለምፀሐይ ደስታ፤ በጠቅላላ ምርጫው በመሳተፍ ድምጻቸውን ለሚፈልጉት ፓርቲ በመስጠት ታሪካዊ አሻራቸውን ማሳረፋቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም የልማት እና የመልካም አስተዳደር ሥራዎችን ለማጠናከር እንደሚሰሩ ገልጸዋል፡፡ የመምረጥ ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ተጠቅመው ለፈለጉት ፓርቲ ድምጻቸውን በመስጠት ሀገራዊ ሃላፊነታቸውን እንደተወጡ የገለጹት ደግሞ በከተማው የአራዳ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ደበበ ባሻ ናቸው። በቀጣይም ለሀገር ዘላቂ ሰላምና ሁለንተናዊ ልማት መጠናከር የበኩላቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል።
በምርጫው ያሳየነውን ንቁ ተሳትፎ በልማት ለመድገም ተዘጋጅተናል
Jun 5, 2026 191
ሐረር ፤ ግንቦት 28/2018 (ኢዜአ) ፦ በምርጫ ወቅት የታየውን ጠንካራ የሕዝብ ተሳትፎና አንድነት በልማት ሥራዎች ላይም በመድገም የሀገራቸውን ዕድገት ለማፋጠን ዝግጁ መሆናቸውን በሐረር ከተማ የሚገኙ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ። ኢዜአ ያነጋገራቸው የሐረር ከተማ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በምርጫው ላይ ያሳዩትን ተሳትፎ በቀጣይ የልማት ስራዎችን በማጠናከር ልማትና እድገትን ማስቀጠል ይጠበቅብናል ብለዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል ወይዘሮ ሙሉነሽ ዋቅቶላ እንዳሉት፤ ምርጫው ህዝቡ በነቂስ በመውጣት ሀገር ወዳድነቱን በግልጽ ያሳየበት ነው። በምርጫ ያሳየነውን ተሳትፎ በማጎልበት እና የልማት ስራዎችን በማስቀጠል መድገም ይጠበቅብናል ብለዋል። መምህር ቶማስ ዱባለ ፤ምርጫው የኢትዮጵያንና የሕዝቦቿን ትልቅ ስኬት ያሳየ ነው ሲሉ አክለዋል። ከዚህም ባለፈ የተጀመሩትን የልማት ስራዎች በማፋጠን ለሀገር ልማት መትጋት ይገባል ሲሉም ገልጸዋል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ታደሰ በየነ በበኩላቸው፤ ምርጫው የህዝቡ የነቃ ተሳትፎ የታየበት፣ የሀገሪቱን የወደፊት ብሩህ ተስፋ ያሳየና የሚያስደስት እንደነበር አስታውሰዋል። በቀጣይም በምርጫው ላይ ያደረጉትን ተሳትፎ በልማት ሥራዎች ላይ በመድገም ለልጅ ልጆቻቸው ብሩህ ሀገርን የማሻገር ተግባር እንደሚያከናውኑ ጠቅሰዋል። ምርጫው በርካታ ዜጎች የተሳተፉበትና ሰላማዊ መሆኑ በእጅጉ እንዳስደሰታቸው የገለጹት ደግሞ መምህር ደረጀ ተስፋዬ ናቸው። መምህር ደረጃ ፤ በቀጣይም ሀገራዊም ሆነ ክልላዊ የልማት ስራዎች ላይ የነቃ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል።
በክልሉ በከተሞች ከ200 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የስራ ዕድል የፈጠሩ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተካሄደ ነው
Jun 5, 2026 134
ባህር ዳር፤ግንቦት 28/2018( ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በከተሞች ከ200 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የስራ ዕድል የፈጠሩ የልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተካሄደ መሆኑን የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ ከተሞችን በኮሪደር ልማት ኢንሼቲቭ የማዘመን፣በቴክኖሎጂ የማላቅና ስማርት የማድረግ ስራ በሰፊው እየተካሄደ እንደሚገኝም ተጠቁሟል። የክልሉ ከተማና መሰረተ ልማት ቢሮ ሃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፥ በክልሉ ከተሞችን ለኑሮና ኢንቨስትመንት ምቹ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። ለዚህም በተለያዩ ከተሞች ከ8 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተካሄደ መሆኑን ተናግረዋል። በከተሞቹ 1 ሺህ 10 የልማት ፕሮጀክቶች ተነድፈው በቅንጅት እየተተገበሩ መሆኑን አመልክተዋል። የልማት ፕሮጀክቶቹ በከተማ አስተዳደሮች በጀትና በህብረተሰቡ ተሳትፎ ግንባታቸው እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመው፥ በፕሮጀክቶቹ ግንባታ ከ200 ሺህ ለሚበልጡ ወገኖች የስራ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል። ከፕሮጀክቶቹ መካከል እስካሁን በተደረገ ጥረት 336 የሚሆኑት ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት መብቃታቸውን ጠቅሰው፤ቀሪዎቹን እስከ በጀት ዓመቱ መጨረሻ ሙሉ በሙሉ ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ከእነዚሁ ፕሮጀክቶች መካከልም 14 ኪሎ ሜትር የጌጠኛ ድንጋይ ንጣፍ መንገድ፣ ከ40 በላይ የተለያየ ደረጃ ያላቸው ድልድዮች፣ ከ80 በላይ ሼዶች እንዲሁም የኤሌክትሪክና የውሃ መስመር ዝርጋታና ሌሎች መሰረተ ልማቶች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል። በመሰረተ ልማት ማስፋፋት ስራ የከተሞችን ሁለንተናዊ ገፅታ በመቀየር ተጨባጭ ለውጥ ማስመዝገብ መቻሉንም አስታውቀዋል።
ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትና የአየር መንገዱን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉ ናቸው
Jun 4, 2026 1768
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2018(ኢዜአ)፦ ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትና የኢትዮጵያ አየር መንገድን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉ መሆናቸውን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሠላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 23ኛ መደበኛ ስብሰባው የተለያዩ አዋጆችን መርምሮ አጽድቋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ (ዶ/ር)፤ ከተለያዩ ሀገራት ጋር የተደረጉት ስምምነቶች የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች እና የአየር መንገዱን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉ ናቸው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከሴራሊዮን ሪፐብሊክ፣ ከአንጎላ ሪፐብሊክ፣ ከባንግላዲሽ ሕዝባዊ ሪፐብሊክ እና ከኢስዋቲኒ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ጋር ያደረገቻቸውን የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ ሪፖርቶችና የውሳኔ ሃሳቦችን ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። እነዚህ የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆች ለንግድና ኢንቨስትመንት፣ ለቱሪዝም፣ ለዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶች እንዲሁም የአየር ትራንስፖርት መዳረሻዎችን ለማስፋፋት ያላቸውን ከፍተኛ ጠቀሜታ አብራርተዋል። በተጨማሪም ስምምነቶቹ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም የሚያስጠብቁና በዘርፉ ያላትን ሚና በማጉላት ተጠቃሚነቷን የሚያሳድጉ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። ምክር ቤቱም በቀረቡት ረቂቅ አዋጆች ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ አዋጆቹን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። ከምክር ቤቱ አባላት በኩልም የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆቹ የአየር መንገዱን ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ጉልህ ሚና እንደሚኖራቸው ተገልጿል። በሌላ በኩል፣ በኢትዮጵያ እና በሩሲያ ፌዴሬሽን መካከል የጋራ የባዮሎጂ ምርምር ማዕከል ለማቋቋም የተፈረመው ስምምነት ረቂቅ አዋጅም በምክር ቤቱ ጸድቋል። የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ (ዶ/ር)፤ ስምምነቱ የሀገሪቱን ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ዕድገት ለማፋጠን፣ ለዓሳ ሀብት ልማት፣ ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን ለማሳደግና በዘርፉ የግል ባለሀብቶችን ለመሳብ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። በተጨማሪም የከፍተኛ ትምህርትና የምርምር ተቋማትን አቅም ለማሳደግና የምርምር ሥራዎችን ወደ ገበያ አውጥቶ ለማቅረብ ያለውን ጠቀሜታም አንስተዋል። በተጨማሪም ምክር ቤቱ በኢትዮጵያ እና በቬትናም ሶሻሊስት ሪፐብሊክ መንግሥት መካከል የዲፕሎማቲክ ወይም ኦፊሻል የአገልግሎት ፓስፖርት ለያዙ ዜጎች ቪዛን ለማስቀረት በተፈረመው የስምምነት ረቂቅ አዋጅ ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ፣ አዋጁን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል።
ስምምነቱ የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል ነው
Jun 4, 2026 474
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያና በአፍሪካ ልማት ባንክ መካከል የተፈረመው ስምምነት የአርብቶ አደሮችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን በ23ኛ መደበኛ ስብሰባው የተለያዩ አዋጆችን መርምሮ አጽድቋል። በምክር ቤቱ የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) በኢትዮጵያና በአፍሪካ ልማት ባንክ መካከል የተፈረመው የአርብቶ አደሮች የኑሮ ዘይቤ ማሻሻያ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውል የብድር ስምምነት እና በኢትዮጵያና በዓለም አቀፍ የልማት ማህበር 6ኛው ምዕራፍ የልማታዊ ሴፍትኔት ማስፈጸሚያ ፕሮጀክት የተደረገ የብድር ስምምነት ረቂቅ አዋጆችን አስፈላጊነት በተመለከተ ለምክር ቤቱ ማብራሪያ አቅርበዋል።   የአርብቶ አደሮች የምግብና የኑሮ ዘይቤ ማሻሻያ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የሚውለው የብድር ስምምነት ከኢትዮጵያ የብድር ስትራቴጂ ጋር የሚጣጣም ነው ብለዋል። ስምምነቱ የአርብቶ አደሮችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ፣ ለግብርና፣ ለመስኖ ልማት፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋምና የአደጋ ተጋላጭነትን መቀነስ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። ለውሃ መሰረተ ልማት፣ ለእንስሳት ጤና አገልግሎት፣ ለዘላቂ የመሬት አያያዝ፣ ለአየር ትንበያ ጣቢያዎችና ለሌሎች መሰረተ ልማቶች ማስፋፊያ እንደሚውልም ጠቅሰዋል። ምክር ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ላይ በጥልቀት ከተወያየ በኋላ ረቂቅ አዋጁን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። በሌላ በኩል በኢትዮጵያና በዓለምአቀፍ የልማት ማህበር 6ኛው ምዕራፍ የልማታዊ ሴፍትኔት ማስፈጸሚያ ፕሮጀክት የተደረገው የብድር ስምምነት ሴቶችና ወጣቶችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን ተናግረዋል።   በተለይም በኑሮ ማሻሻል፣ በምግብ ዋስትና እና በማህበራዊ ጥበቃ ሰርዓት እየተከናወኑ ካሉ ብሔራዊ የልማት ፕሮጀክቶች ጋር የተናበበ በመሆኑ ሚናው የጎላ ነው ብለዋል። የምክር ቤቱ አባላት የብድር ስምምነቶቹ በግብርና፣ በመስኖ ልማት፣ በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋምና የአደጋ ተጋላጭነትን በመቀነስ የዜጎችን ኑሮ ለማሻሻል የተጀመሩ ሥራዎችን እንደሚያጠናክሩ ጠቁመዋል። ስምምነቶቹ በአግባቡ እንዲተገበሩና የታለመውን ግብ እንዲያሳኩ ድጋፍና ክትትል ማድረግ እንደሚገባም ተናግረዋል። ምክር ቤቱ የስምምነት ረቂቅ አዋጆች ላይ በዝርዝር በመወያየት በአብላጫ ድምጽ አጽድቋቸዋል። በሌላ በኩል የፌዴራል ታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅን፣ የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅን፣ የምግብ ስርዓትና ስርዓተ ምግብ ረቂቅ አዋጅን፣ የኢትዮጵያ የካርበን ገበያ ረቂቅ አዋጅን እና የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ ረቂቅ አዋጆች ቀርበው ውይይት ከተደረገባቸው በኋላ ለሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴዎች ተመርተዋል።
በበጀት ዓመቱ የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የተጀመሩ ተግባራትን ለማጠናቀቅ በትኩረት ይሰራል
Jun 4, 2026 450
አዲስ አበባ፤ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ)፦በ2018 በጀት ዓመት የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የተጀመሩ ተግባራትን ለማጠናቀቅ በትኩረት ይሰራል ሲሉ በብልፅግና ፓርቲ የሀረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሀላፊ አቶ ጌቱ ወዬሳ ገለጹ። በሀረሪ ክልል በ2018 በጀት ዓመት ቀሪ ጊዜያት በሚከናወኑ ተግባራት ላይ ውይይት ተደርጓል።   በብልፅግና ፓርቲ የሀረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሀላፊ አቶ ጌቱ ወዬሳ በውይይቱ ላይ እንደገለፁት፥ የበጀት ዓመቱ ቀጣይ እቅዶችን በስኬት ለማጠናቀቅ በትኩረት ይሰራል። በመሆኑም ተቋማት የማህበረሰቡን የመልካም አስተዳደርና ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የጀመሯቸውን ተግባራት በቀሪ ጊዜያት ለማጠናቀቅ በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ ገልፀዋል። በተለይም በቱሪዝም ልማት፣የትምህርትና የጤና አገልግሎት ጥራትና ተደራሽነትና በኮሪደር ልማት ላይ የተመዘገቡ አበረታች ውጤቶችን አጠናክሮ ማስቀጠል ልዩ ትኩረት እንደሚሰጠው ገልፀዋል።   የሌማት ትሩፋት እና የከተማ ግብርና ስራዎችን በማጠናከር የግብርና ምርትና ምርታማነትን የማሳደጉ ስራም በበጀት ዓመቱ በልዩ ትኩረት ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆናቸውን አስገንዝበዋል። ለዜጎች የስራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት በመስጠት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው እንዲጎለብት ለማድረግ በቀጣይ ርብርብ እንደሚደረግም ገልፀዋል።
የባህርዳር ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከጣና ውበት ጋር በማሰናሰል የተገነባ ዘመን ተሻጋሪ የቱሪዝም ሃብት ነው
Jun 4, 2026 450
ባህር ዳር ፤ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ) ፡-የባህርዳር ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከጣና ውበት ጋር በማሰናሰል የተገነባ ዘመን ተሻጋሪ የቱሪዝም ሃብት መሆኑን የከተማዋ ነዋሪዎች ተናገሩ። ‎‎ከተማዋ በተፈጥሮ የታደለችና አባይና ጣናን ተንተርሳ መመስረቷ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች ይበልጥ ውበቷ እየተገለጠ እንድትመጣ አድርጓታል። የከተማዋ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ትዕግስት አበጀ፤ ባህር ዳር ከተማ በተፈጥሮ የታደለች መሆኗን ተከትሎ ባለፉት ጥቂት አመታት ደግሞ ውበቷን የገለጡ የልማት ስራዎች መከናወናቸው ውበቷን ያጎላው መሆኑን ገልጸዋል።   በከተማዋ ከኮሪደር ልማቱ በተጨማሪ የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ በርካታ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን አንስተው ውበቷና ድምቀቷ ይበልጥ እየጨመረ መጥቷል ብለዋል። የባህር ዳር የኮሪደር ልማት ከጣና ሃይቅ ጋር በተሳሰረ መልኩ የተገነባ መሆኑም ከተማዋን ልዩ ገፅታ ስለማጎናፀፉ አንስተዋል። እንደ አጠቃላይ የባህርዳር ከተማ የኮሪደር ልማት ከተማዋን ከጣና ውበት ጋር በማሰናሰል የተገነባ ዘመን ተሻጋሪ የቱሪዝም ሃብት መሆኑን ገልጸዋል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ ወጣት ደጀኔ አለምነው፤ የባህር ዳር ውበትና የቱሪዝም መስህብነት ከእለት ወደ እለት እያደገ መሆኑን ተናግሯል።   ‎በከተማዋ የኮሪደር ልማቱን ተከትሎ የተለያዩ የመዝናኛ ስፍራዎች፣ የአረንጓዴ ልማት፣ የእግረኛ፣ የሳይክል መንገዶችና ዘመናዊ የመንገድ ዳር መብራቶች መዘጋጀታቸው ከተማዋን ለነዋሪዎችና ለቱሪስቶች ምቹ አድርጓታል ብሏል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ገብረስላሴ ሳህሌ፤ ከባህር ዳር ከተማ ለዘመናት ተከልሎ የነበረው የጣና ሃይቅ ውበት በኮሪደር ልማት መገለጡ ለነዋሪዎችም ይሁን ለጎብኝው ደስታ ፈጥሯል ብለዋል። ‎አሁን ላይ ወደ ባህር ዳር ጎራ የሚል ሁሉ ከተማዋን እየጎበኙ የጣናን ውበት እያደነቁ የሚደሰቱበት ስለመሆኑ ተናግረዋል።   ባለፉት ጥቂት ዓመታት በባህር ዳር የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎችም የተገነቡ ሰው ተኮር የልማት ስራዎች የሚደነቁ ናቸው ብለዋል።
ምክር ቤቱ የአየር አገልግሎት ረቂቅ አዋጆችን መርምሮ አጸደቀ
Jun 4, 2026 244
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ)፡- የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 23ኛ መደበኛ ስብሰባ ኢትዮጵያ ከተለያዩ ሀገራት ጋር ያደረገቻቸውን የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆች መርምሮ አጸደቀ። የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማሕዲ (ዶ/ር) የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆችን ሪፖርትና የውሳኔ ሐሳቦች ለምክር ቤቱ አቅርበዋል፡፡   በዚሁ ወቅትም፤የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጆቹ ኢንቨስትመንትን በመሳብና የአየር ትራንስፖርት መዳረሻዎችን በማስፋት ለሀገራችን የአየር ትራንስፖርትና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ያላቸው ሚና ወሳኝ ነው ብለዋል።   ከአየር አገልግሎት ስምምነቶቹ መካከልም በኢትዮጵያ መንግሥትና እና በሴራሊዮን መንግሥት በኩል የተፈረመው አንዱ መሆኑን ጠቁመው፤ ስምምነቱ ለአየር መንገዶች ወደ ተመረጡ መዳረሻዎች በቀጥታ ለማረፍና ምቹ የአቪዬሽን አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚያስችል አስገንዝበዋል። ይህን የአየር አገልግሎት ረቂቅ አዋጅም፤ ምክር ቤቱ አዋጅ ቁጥር 1417 /2018 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡ በተመሳሳይ በአንጎላ ሪፐብሊክ እና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከል የተፈረመው የአየር አገልግሎት ስምምነት ረቂቅ አዋጅ ለምክር ቤቱ የቀረበ ሲሆን፤ ስምምነቱ በሀገራቱ መካከል ያለውን በርካታ ዓመታት ያስቆጠረ ግንኙነት ለማሳደግ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መረጃ እንዳመላከተው፤ ይህ ረቂቅ አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1418 /2018 ሆኖ በሙሉ ድምጽ ፀድቋል። በሌላ በኩል በኢትዮጵያ መንግሥት እና በባንግላዴሽ መካከል የተደረገው የአየር አገልግሎት ስምምነት በሀገራቱ መካከል እያደገ የመጣውን የአየር ትራንስፖርት ፍሰት ከግምት ያስገባ መሆኑንም ነው ያነሱት። አክለውም፤ የውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ለመሳብ፣ በንግድ፣ ቱሪዝም እና የውጪ ምንዛሬ ለሀገራችን በማስገኘት ረገድ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል፡፡ በዚህም መሠረት ምክር ቤቱ ይህን ረቂቅ አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1419/ 2018 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡ ሌላው በምክር ቤቱ የጸደቀው የአየር አገልግሎት ረቂቅ አዋጅ፤ በኢትዮጵያ መንግሥት እና በኢስዋቲኒ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት መካከል የተደረገው ስምምነት ነው። ይህም ያለ በረራ ድግግሞሽ ገደብ የጭነት በረራዎችን ማከናወንን ጨምሮ ለበረራ የሚያስፈልጉ ቁሳቁሶችን ከጉምሩክ ቀረጥ ነፃ ማስገባትን የሚያካትት በመሆኑ፤ የበረራ ወጪን እንደሚቀንስ አስረድተዋል። በተመሳሳይ ምክር ቤቱ ይህን ረቂቅ አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1420/2018 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡ የአየር አገልግሎት ስምምነቶቹ፤ የኢትዮጵያን ጥቅም የሚያስጠብቁና በዘርፉ በቀጣናው ያላትን ሚና በማጉላት ተጠቃሚነቷን የሚያሳድጉ መሆናቸው ተመላክቷል።
በክልሉ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግ ስራ እየተከናወነ ነው
Jun 4, 2026 288
ጋምቤላ፤ ግንቦት 27/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል የቡና አብቃይ ወረዳዎች የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ለአርሶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የጋምቤላ ክልል ለግብርና ኢንቨስትመንትና ለተለያዩ ሰብሎች ልማት ምቹ የአየር ንብረትና ሰፊ ለም መሬት ካላቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች አንዱ ቢሆንም፣ የቡና ልማት ዘርፉ ግን ካለው ከፍተኛ እምቅ አቅም አንጻር በተገቢው ሳይለማ ለረጅም ዓመታት ቆይቷል። በተለይም እንደ ጋዶ፣ የጎደሬ ወረዳን ጨምሮ አንዳንድ የምዕራብ አኙዋክ አካባቢዎች ለቡና ልማት እጅግ ተስማሚ የተፈጥሮ ስነ-ምህዳር አለው። በእነዚህ ወረዳዎች የተራቆቱ አካባቢዎችን ከአረንጓዴ አሻራ ልማት ጋር በማቀናጀት በቡናና ጥምር የጥላ ዛፍ በመሸፈን ስነ-ምህዳርን በማሻሻልና የዘርፉን ምርታማነት በመጨመር ረገድ ውጤታማ ስራዎች እየተከናወኑ ነው።   የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንድሮው ቱት ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ በማጃንግ ዞን በሚገኙ የመንጌሽና የጎደሬ ቡና አብቃይ ወረዳዎች የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ተደራሽ በማድረግ የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው። የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ ነባር ዝርያዎችን በተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች በመተካትና በተራቆቱ አካባቢዎች የቡና ጥምር ደን ልማትን በማስፋት ምርታማነትን የማሳደግ ስራ እንደሚከናወን ነው የገለጹት። በዘንድሮው ክረምት ከአረንጓዴ አሻራ ልማቱ ጋር በማቀናጀት በፕሮጀክቶች፣ በባለሃብቶችና በአርሶ አደሮች ከ4 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞች መዘጋጀታቸውን አቶ አንድሮው ተናግረዋል።   በቢሮው የምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ ሀብታሙ ገዳሙ እንዳሉት የተሻሸሉ የቡና ዝርያዎችን ከቴፒና ከጅማ ግብርና ምርምር ተቋማት በማምጣት ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግ ተግባር እየተከናወነ ነው። በምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራሙ ባለፉት ሁለት ዓመታት በተለይም በጎደሬ ወረዳ በሞዴል አርሶ አደሮች በኩታ ገጠም የቡና ማሳና በሰርቶ ማሳያዎች የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን የማስፋትና የማስተዋወቅ ስራ ሲከናወን መቆየቱን ገልጸዋል። በዘንድሮው ክረምትም ከ250 ሺህ የሚበልጡ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በኩታ ገጠም ለሚያለሙና ለሌሎች ሞዴል አርሶ አደሮች ለማሰራጨት ችግኞቹ መዘጋጀታቸውን አቶ ሀብታሙ ተናግረዋል። በማጃንግ ዞን ጎደሬ ወረዳ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች ካገኙ አርሶ አደሮች መካከል አቶ ዝናቤ ቢለው በሰጡት አስተያየት በተራቆቱ አካባቢዎች የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ከጥምር የደን ዛፍ ጋር አቀናጅቶ በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በቀጣይም በተመሳሳይ መልኩ የቡና ጥምር ደን ልማቱን በማስፋትና ተጠቃሚ ለመሆን እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በምግብ ስርዓት ማጠናከሪያ ፕሮግራም ድጋፍ የተራቆቱ አካባቢዎችን በቡናና በጥምር የጥላ ዛፍ በማልማት አካባቢውን ወደ ነበረበት በመመለስና ከዘርፉም ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ ሌላው የዚሁ ቀበሌ አርሶ አደር አቶ ከድር ሙሀመድ ናቸው።    
በአሶሳ ከተማ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት የከተማዋን እንቅስቃሴ አቀላጥፏል
Jun 4, 2026 271
አሶሳ፤ ግንቦት 27/2018(ኢዜአ)፦ በአሶሳ ከተማ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት የከተማዋን የትራፊክ ፍሰትና አጠቃላይ እንቅስቃሴ ለማቀላጠፍ ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የከተማዋ ነዋሪዎች ተናገሩ። በአሶሳ ከተማ እየተካሄደ ያለው የኮሪደር ልማት፤ የከተማዋን መሠረተ ልማት ለማዘመን፣ የነዋሪዎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻልና ከተማዋን ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ሳቢ ለማድረግ ታስቦ የተጀመረ ሰፊ መርሃ ግብር ነው። በአንደኛው ዙር የተከናወኑት ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን ተከትሎ፣ አሁን ላይ ትኩረቱን የንግድና ማህበራዊ አገልግሎት ማዕከላትን ማዘመን ላይ ያደረገው ሁለተኛው ዙር ስራ በስፋት እየተገነባ ይገኛል። የሁለተኛው ዙር የኮሪደር ልማት፣ ዘመናዊ የአገልግሎት መስጫ ማዕከላትን ብቻ ሳይሆን ምቹ የእግረኛና የተሽከርካሪ መንገዶችንም በማካተት የከተማዋን ገጽታ እየቀየረ ይገኛል። አስተያየታቸውን የሰጡን የከተማዋ ነዋሪዎች እንደገለጹት፣ የእግረኛ እና የተሽከርካሪ መንገዱ ተለይቶ መሰራቱ የትራፊክ ፍሰቱን በእጅጉ አቅልሎታል።   ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል አቶ ማስረሻው አራጌ እንዳሉት፣ ከዚህ ቀደም የነበረው መንገድ ጠባብ ከመሆኑ የተነሳ ለተሽከርካሪም ሆነ ለእግረኞች ምቹ እንዳልነበር አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት ግን በኮሪደር ልማቱ ለሁሉም ምቹ መንገድ በመፈጠሩ፣ የትራፊክ እንቅስቃሴው መሳለጡን አቶ ማስረሻው ተናግረዋል። ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ የሺወርቅ ንብረት፤ የኮሪደር ልማቱ ከተማዋን በሁሉም መስክ ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትሆን አድርጓታል ብለዋል።   በተለይም በሁለተኛው ዙር እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት፣ በእግረኞች ላይ ይደርስ የነበረውን የትራፊክ አደጋ በመቀነስ ረገድ አይነተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። በከተማዋ የባጃጅ አሽከርካሪ የሆነው አህመድ ሰኢድ በበኩሉ የኮሪደር ልማቱ ለአሸከርካሪዎች ነፃነትን የሰጠ እና ለተሽከርካሪዎችም ምቹ መሆኑን ተናግሯል።   የኮሪደር ልማቱ ለአሸከርካሪዎች እና እግረኞች የፈጠረው ምቹ ሁኔታ የትራፊክ አደጋን ከመቀነስ አንፃር ትልቅ ትርጉም አለው ያሉት ደግሞ በአሶሳ ከተማ የትራፊክ ተቆጣጣሪ ምክትል ሳጅን ኢዘዲን አልበሽር ናቸው።   የኮሪደር ልማቱ የትራፊክ ተቆጣጣሪዎችን የሥራ ጫና የቀነሰ እና የተቀላጠፈ የትራፊክ እንቅሰቃሴ እንዲፈጠር አይነተኛ ሚና ያበረከተ መሆኑን ጠቁመዋል።    
የሚያዝያ እና ግንቦት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ቁልፍ ተግባራት ቅኝት ከምስል ጋር!
Jun 3, 2026 801
  የኢንዱስትሪ መስፋፋት እና ኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነት:- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ነጻነት ለማረጋገጥ፣ የረጅም ጊዜ የኢንዱስትሪ እድገትን እና ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ መተካትን መሰረት ያደረጉ የተለያዩ የአምራች ዘርፉ እንቅስቃሴዎችን በንቃት መርተዋል፤ በዚህም የፋይናንስ አቅርቦትን ማሳደግ ላይ ያተኮረውን 4ኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ በይፋ የከፈቱ ሲሆን፣ የወጣቶችን የስራ እድል ለማስፋፋትም በአዲስ ኣበባ የሚገኘውን የገላን ጉራ ኢንዱስትሪ ፓርክ መርቀው ከፍተዋል። በተጨማሪም የታዳሽ ሃይል አቅምን ለማሳደግ አዲስ ስራ የጀመረውን የጎበዜ የሶላር ሴል ማምረቻ ፋብሪካን እንዲሁም፣ የአካባቢውን ጥሬ እቃዎች በመጠቀም የገቢ ምርቶችን ለመተካት ያለመውን በሞጆ ከተማ የሚገኘውን የግራንደር የሴራሚክ ማምረቻ ፋብሪካንም መርቀው ከፍተዋል።   የላቀ የጤና ስርዐትና ዘመናዊ አገልግሎቶች:- ኢትዮጵያ በልዩና በላቀ የህክምና ብቃት ቀጣናዊ ማዕከል ለመሆን የምታደርገውን ስትራቴጂካዊ ጉዞ ግብ ለማሳካት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እጅግ በዘመኑ የህክምና ቴክኖሎጂዎች እና በሮቦቲክስ የታገዘውን እንዲሁም የካንሰር እና የልብና ህመሞችን በሀገር ውስጥ ለማከም የተገነባው ዘመናዊውን የላፍቶ ሆስፒታል በአዲስ አበባ በይፋ መርቀው ከፍተዋል፤ በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ውስጥ የህክምና ስልጠና ላይ ለሚገኙ የሩዋንዳ እና ከሌሎች አፍሪካ ሀገራት ለመጡ የህክምና ባለሙያዎች ይፋዊ የእራት ግብዣ አድርገዋል።   መሰረተ ልማት፣ ዘላቂ አገልግሎቶች እና ትራንስፖርት:- ጠቅላይ ሚኒስትሩ የንግድና ማህበራዊ ትስስርን የሚጠናክረውንና የኢትዮጵያ አየር መንገድ 24ኛ የአገር ውስጥ መዳረሻ የሆነውን አዲሱን የነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ መርቀዋል፤ በተጨማሪም በጎመሌ ወረዳ የሚገኘውን የደሴ ጎራ ግድብን ጨምሮ የፊና ኦሮሚያ መስኖ ፕሮጀክቶች መጠናቀቃቸውን የተከታተሉ ሲሆን ንጹህ ውሃ ለማቅረብና ለረጅም ጊዜ የሚዘልቅ የድርቅ መቋቋም አቅምን ለመገንባት የተነደፈውን መጠነ-ሰፊ የቦረና የውሃ አቅርቦት ፕሮጀክት ማስፋፊያ ስራ ጉብኝትንም በበላይነት መርተዋል።   የግብርና ትራንስፎርሜሽን እና የምግብ ሉዓላዊነት:- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የክላስተር እርሻን ለማስፋፋት በዋና ዋና የግብርና ክልሎች የመስክ ጉብኝት ያደረጉ ሲሆን በዚህም የሀገር ውስጥ የዩሪያ ማዳበሪያ ምርትን ለማሳደግ የታቀደውን የፋብሪካ ግንባታ ሂደት ለመገምገም ከአሊኮ ዳንጎቴ ጋር ወደ ጎዴ ተጉዘዋል። በተጨማሪም በምስራቅ ቦረና ዞን በሺዎች የሚቆጠሩ አባወራዎችና እማወራዎችን ያሳተፈውን መጠነ ሰፊ የክላስተር ግብርና ንቅናቄ የጎበኙ ሲሆን በሰሜን ሸዋ ዞን በብዙ ሄክታር መሬት ላይ የሚገኘውን የስንዴ እርሻ ልማትም ጎብኝተዋል።   የሚዲያ እና የብሔራዊ ፖሊሲ ሉዓላዊነት:- የመንግሥት ተቋማትን እና የብሔራዊ ፖሊሲ ነጻነትን ለማጠናከር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀገራዊ የምክክር መድረኮች ላይ ተገኝተዋል። ዲጂታላይዝድ ወደሆነ እና ራሱን ወደቻለ የስታቲስቲክስ ማዕቀፍ የሚደረገውን ሀገራዊ ሽግግር ለመደገፍ "የመረጃ ሉዓላዊነት ለፖሊሲ ነጻነት" በሚል መሪ ቃል በተዘጋጀው ብሔራዊ ጉባኤ ላይ የተገኙ ሲሆን፤ በተጨማሪም የብሔራዊ ምክክር ኮሚሽን ወደ ትግበራ ምዕራፍ ሊሸጋገር የቀረበውን ይፋዊ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ተቀብለዋል። በዚሁ ወር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለብሔራዊ ልማት የሚረዱ የሚዲያ ስነ-ምግባር ሙያዊ መመሪያዎችን አስምረው የተናገሩበት እና “የሚዲያ እመርታ ለሀገር ግንባታ” በተሰኘው ብሔራዊ መድረክ ላይ ለሚዲያ ዘርፍ መሪዎች እና ባለሙያዎች ንግግር አድርገዋል። የባህል ጥበቃ እና አከባቢያዊ እንክብካቤ:- በኦሮሚያ ክልል የገዳ ሥርዓት ታሪክንና ፍልስፍናን ለመጠበቅ በያቤሎ ከተማ የተገነባውን የቦረና ባህል ማዕከል ጠቅላይ ሚኒስትሩ መርቀው የከፈቱ ሲሆን ማዕከሉ በመደመር መጽሐፍ ሽያጭ ገቢ የተደገፈ እንደሆነም ይታወሳል። ከዚህ ጎን ለጎን፣ የዱር እንስሳትና ብዝሃ-ሕይወት መጠበቂያ ሆኖ የሚያገለግለውን የቦረና ብሔራዊ ፓርክ መርቀው ከፍተዋል።   ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ እና የሁለትዮሽ ግንኙነቶችን የሚያጠናክሩ ማዕቀፎች:- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን ዲፕሎማሲያዊ አጋርነት ለማጠናከር በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ከፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር የተወያዩ ሲሆን በብድር እና ተለያዩ ዘርፎች አጋርነት ላይ ስምምነቶችን አድርገዋል። በተጨማሪም በናይሮቢው አፍሪካ ፎርዋርድ ጉባኤ ላይ የተሳተፉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ኢትዮጵያ ከተገበረቻቸው የልማት ሞዴሎች ልምድ ከማካፈላቸውም ባለፈ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (IMF) ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክሪስታሊና ጆርጂየቫ ጋር የኢኮኖሚ ምክክር አድርገዋል። በዚሁ ወር በጅቡቲ የፕሬዚዳንት እስማኤል ዑመር ጌሌን በዓለ-ሲመት የታደሙ ሲሆን ከኔዘርላንድስ ጠቅላይ ሚኒስትር ሮብ ዬተን ጋር የስልክ ውይይት አድርገዋል። በመጨረሻም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት 80ኛ ዓመት መታሰቢያ ምክንያት በማድረግ የቴምብር ስብስብ ይፋ አድርገዋል።
በሐረሪ ክልል 11 ሺህ 956 ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ ነው
Jun 3, 2026 630
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በበልግ እና መኸር እርሻ በድምሩ 11 ሺህ 956 ሄክታር መሬት በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታውቋል። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የግብርና ልማት ቢሮ ኃላፊ ሮዛ ኡመር እንደገለፁት በክልሉ ያለውን አነስተኛ መሬት በአግባቡ ተጠቅሞ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀናጀ ስራ እየተሰራ ይገኛል። በክልሉ በ2018/19 በበልግ እና መኸር እርሻ በድምሩ 11 ሺህ 956 ሄክታር መሬት በተለያዩ የሰብል ዓይነቶች ለማልማት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በበልግ ዝናብ እስካሁን 8 ሺህ 681 ሄክታር መሬት በዘር መሸፈኑን ጠቁመው፥ ቀሪው 3 ሺህ 275 ሄክታር በክረምት መኽር ዝናብ ቶሎ ደራሽ ማሽላ እና ስንዴ ለመዝራት አሰፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። በክልሉ ሶስት የገጠር ወረዳዎች በሚገኙ ማሳዎች ላይ እየለሙ የሚገኙት ሰብሎችም ማሽላ፣ በቆሎ እና ስንዴ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ለመኸር እርሻው ምርትና ምርታማነት ማደግ አስፈላጊው የማዳበሪያ፣ የዘርና ሌሎች የግብርና ግብዓት አቅርቦት ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ያመለከቱት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሯ በምርት ዘመኑ እየለሙ ካሉ ሰብሎች 300 ሺህ ኩንታል ምርት ለመሰበሰብ መታቀዱንም አስረድተዋል። በየደረጃው ያሉ የግብርና ባለሙያዎችም ለአርሶ አደሩ አስፈላጊውን ሙያዊ እገዛና ድጋፍ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም አርሶ አደሩን ከዝናብ ጠባቂነት ከማላቀቅና ተጠቃሚነትን ከማሳደግ አንፃር አበረታች ስራዎች ተከናውነዋል ነው ያሉት። በቀጣይም የተገኙ አበረታች ውጤቶችን በማስቀጠል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማጎልበትና ምርት እና ምርታማነትን ለማሳደግ የላቀ ትኩረት እንደሚሰጥ ገልጸዋል።
የሀገር ሉዓላዊነትና ነጻነት በምልዐት የሚረጋገጠው በጥራት፣ በዓይነት እና በብዛት የኢንዱስትሪ ምርቶችን ማምረት ስንችል ነው
Jun 3, 2026 630
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 26/2018(ኢዜአ)፦የሀገር ሉዓላዊነትና ነጻነት በምልዐት የሚረጋገጠው በጥራት፣ በዓይነት እና በብዛት የኢንዱስትሪ ምርቶችን በራስ ዕውቀት፣ በራስ ክህሎት እና በራስ ቴክኖሎጂ ማምረት ስንችል ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤የሀገር ሉዓላዊነትና ነጻነት በምልዐት የሚረጋገጠው በጥራት፣ በዓይነት እና በብዛት የኢንዱስትሪ ምርቶችን በራስ ዕውቀት፣ በራስ ክህሎት እና በራስ ቴክኖሎጂ ማምረት ስንችል ነው ብለዋል፡፡ መንግሥትም በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉ የታለመውን ዘላቂ ዕድገት እና ተወዳዳሪነት ለማረጋገጥ ፖሊሲዎችን ማሻሻሉን፡ አሠራሮችን መዘርጋቱን እና ማበረታቻዎችን ማድረጉን ገልጸዋል። የዚህ ሪፎርም አካል የሆነው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄም ፍሬው በግልጽ እየታየ መሆኑን ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም