ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በክልሉ የምርጥ ዘር አቅርቦትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 2, 2026 499
ጂንካ፤ሰኔ 25/2018(ኢዜአ):- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የምርጥ ዘር አቅርቦትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማረጋገጥ ትኩረት መስጠቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡ የክልሉ ምርጥ ዘር ድርጅት በአሪ ዞን በደቡብ አሪ ወረዳ ጨለጎድ ቀበሌ ለምርጥ ዘር ብዜት የሚውል 1 ሺህ ሄክታር መሬት ተረክቧል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ግዳልቅ አልቅሚ በወቅቱ እንደገለፁት፤ በክልሉ ግብርናውን በማዘመን ምርትና ምርታማነትን ለማሻሻል ለምርጥ ዘር ብዜት ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል። የምርጥ ዘር ብዜቱን በማስፋት የክልሉን ፍላጎት ከመሸፈን ባለፈ ለሌሎች ክልሎች ለመትረፍ የተጨማሪ መሬት ርክክብ መከናወኑን ገልጸዋል። በክልሉ የምርጥ ዘር አቅርቦትን በማሻሻል የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን ያመለከቱት ደግሞ የክልሉ ምርጥ ዘር ድርጅት ኃላፊ አቶ ብርሃኑ ግዛው ናቸው። ድርጅቱ በተለያዩ ማዕከላትና በአርሶ አደሮች ማሳ ላይ ምርጥ ዘር እያለማ መሆኑን አንስተው፤ ዛሬ ርክክብ የተደረገው መሬትም በቀጣይ የምርጥ ዘር አቅርቦት ሽፋኑን ለማሳደግ እየተደረገ ላለው ጥረት ትልቅ አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። የአሪ ዞን አስተዳደር ተወካይ አቶ አፌዶ ወርቁ በበኩላቸው፤ በክልሉ የተጀመረው የምርጥ ዘር ብዜት ንቅናቄ በዞኑ ያለውን የምርጥ ዘር አቅርቦት እንደሚያሰፋው ጠቅሰዋል። ዛሬ ርክክብ የተካሄደበት መሬትም የግብርና ቴክኖሎጂ ሽግግርን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነትና የስራ ዕድል ፈጠራን የሚያጠናክር መሆኑን ጠቁመዋል። በወረዳው በደጋማ አካባቢዎች የስንዴ ምርጥ ዘር ብዜት በአርሶ አደር ማሳና በኮርፖሬት ኢንቨስትመንት በስፋት እየተከናወነ እንደሚገኝ የተናገሩት ደግሞ የደቡብ አሪ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ እና የግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አሸናፊ ደኢዶቆ ናቸው። በዚህ የምርጥ ዘር ብዜት መሬት ርክክብ ስነ-ስርዓቱ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በገጠር ኮሪደር፣በፍራፍሬ ልማትና በአግሮ-ኢንዱስትሪ የተጀመሩ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ናቸው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 2, 2026 568
አዲስ አበባ፤ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ)፡- በገጠር ኮሪደር እና የፍራፍሬ ምርትን በአግሮ-ኢንዱስትሪ በማቀነባበር እሴት የተጨመረበት ምርት ወደ ገበያ ለማቅረብ የተጀመሩ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ናቸው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለፁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በጋሞ ዞን ምዕራብ አባያ ወረዳ እየተከናወነ ያለውን የገጠር ኮሪደር ልማት እና ሌሎች የልማት ሥራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጉብኝታቸው ወቅት በገጠር ኮሪደር፣ በግብርና እና በኢንዱስትሪ ዘርፍ የተመዘገቡ ስኬቶችን አስመልክተው ማብራሪያ ሰጥተዋል። ባለፈው ዓመት በመንግስት በኩል ሞዴል መንደሮችን መገንባቱን አስታውሰው፥ አርሶ አደሩ ሞዴል መንደሮችን በራሱ አቅም እንዲገነባ ማበረታቻ ሲደረግ እንደነበር አስታውሰዋል።   ዘንድሮ በምዕራብ አባያ ወረዳ የታዩት የገጠር ኮሪደር ሥራዎች ሙሉ በሙሉ በአርሶ አደሩ አቅምና ወጪ የተገነቡ መሆናቸውን ገልጸዋል። መንግስት የማሰልጠን እና የጡብ ማሽነሪዎችን የማቅረብ ድጋፍ ብቻ ማድረጉን ጠቁመው፥ አርሶ አደሮች ከሙዝ ሽያጭ ባገኙት ገቢ ዘመናዊና ምቹ ቤቶችን መገንባት መቻላቸውን አድንቀዋል። እነዚህ አዳዲስ የገጠር ኮሪደር ቤቶች የኤሌክትሪክ መብራትና ሌሎችም መሠረተ ልማቶች ያላቸው ሲሆን በጓሯቸውም ፍራፍሬ፣ ዶሮ፣ አሳ፣ ማርና የእንስሳት እርባታን ያካተቱ ናቸው ብለዋል። ይህም አርሶ አደሩ ንጹህ ኑሮ እንዲኖር የሚያስችል፣የምግብ ዋስትናንና ጤናን የሚያረጋግጥ መሆኑን ተናግረዋል።   ይህ ሥራ የዜጎችን ህይወትና የአኗኗር ዘይቤን ይቀይራል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በሁሉም አካባቢ ሲስፋፋ ኢትዮጵያን ወደ ምናስበው ከፍታ የመውሰድ አቅም አለው ብለዋል። በአርባ ምንጭ አካባቢ የፍራፍሬ ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎች ግንባታ መጀመሩን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ እነዚህ ፋብሪካዎች ማቀነባበር ሲጀምሩ ፍራፍሬዎችን በጥሬው ከመላክ ባለፈ የጭማቂ ምርቶችን ለገበያ በስፋት ማቅረብ እንደሚያስችሉ ተናግረዋል። በተጨማሪም በሌማት ትሩፋት ዘርፍ የእርጎና ወተት ማቀነባበሪያዎች ስራ ሲጀምሩ ምርቶቹን እሴት ጨምሮ ወደ ከተሞች ለማቅረብ ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል። በግብርና፣ በገጠር ኮሪደር እና የፍራፍሬ ምርትን ከአግሮ-ኢንዱስትሪ ለማስተሳሰርና እሴት ለመጨመር እየተደረጉ ያሉ ሙከራዎች ተስፋ ሰጪ መሆናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቅሰዋል።
አርሶ አደሩ የክረምት ዝናብና የእርጥበት እቀባን በመጠቀም ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን መዝራት አለበት
Jul 2, 2026 285
ደሴ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ)፡-አርሶ አደሩ የክረምቱን ዝናብ እና የእርጥበት እቀባን በመጠቀም ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን ሊዘራ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የምስራቅ አማራ ማዕከል አስታወቀ። ማዕከሉ የ2018 ዓ.ም ክረምት ወቅት የዝናብ ስርጭትን በማስመልከት መከናወን ባለባቸው ጉዳዮችና ጥንቃቄዎች ላይ በደሴ ከተማ ከባለድርሻ አካላት ጋር መክሯል። በመድረኩ የምስራቅ አማራ ሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ይመር መሀመድ እንደገለጹት፣ የክረምት ዝናብ መደበኛና ከመደበኛ በታች እንደሚሆን የአየር ትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ።   አርሶ አደሩ የክረምትን ዝናብ ውሀ በማሰባሰብ ለልማቱ መዋልና ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን መዝራት እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል። ይህን የግብርና መረጃ ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ ከመፍጠር ባለፈ ግብዓት በወቅቱ በማቅረብ መደገፍ ያስፈልጋል ብለዋል። በማዕከሉ የትንበያና ቅደመ ማስጠንቀቂያ ዴስክ ኃላፊ ወይዘሮ ሉባባ መሀመድ በበኩላቸው፣ በምስራቅ አማራ ቀጠና የ2018 ዓ.ም ክረምት ዝናብ ቀድሞ ሊወጣ እንደሚችል ገልጸዋል። ለዚህም የዘር ሥራውን ፈጥኖ መጀመርና የጎርፍ ውሃን አሰባስቦ እርጥበትን በማቀብ ለደረቃማ ቀናት መጠቀም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።   ፈጥነው የሚደርሱና ድርቅ የሚቋቋሙ የሰብል ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማነትን ማሳደግ እንደሚገባም ገልጸዋል። አርሶ አደሩም የግብርና ባለሙያዎችን ምክር በመተግበር ሰብሉን ከቅጽበታዊ ጎርፍ፣ በሽታና ተባይ መጠበቅ አለበት ብለዋል። የክረምት ዝናብን በአግባቡ በመጠቀም፣ ውሃ በማሰባሰብ፣ ፈጥነው የሚደርሱ ሰብሎችን በመዝራት ምርታማነትን ለማሳደግ ቅደመ ዝግጅት መደረጉን የገለጹት ደግሞ በደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ባለሙያ አቶ ወንድይፍራው ጎቾ ናቸው።   በዞኑ የዝናብ እጥረት ሊከሰትባቸው የሚችሉ ወረዳዎች ተለይተው ፈጥኖ የሚደርስ ምርጥ ዘር እንዲቀርብ እየተደረገ ነው ብለዋል። እንደ ባለሙያው ገለጻ በዞኑ 437 ሺህ ሄክታር መሬት በማልማት 16 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለማግኘት ዝግጅት ተደርጎ ወደተግባር ተገብቷል። የኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ደጀኔ ከበደ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የትንበያውን ምክረ ሀሳብ በመውሰድ አርሶ አደሩ ሰብሉን ቀድሞ እንዲዘራ ተደርጓል።   በዚህም በተያዘው የመኸር ወቅት ከሚለማው 58 ሺህ ሄክታር መሬት ከ27 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በዘር መሸፈኑን ጠቁመው፣ ቀሪውን ፈጥኖ በሚደርሱ ሰብሎች ለመሸፈን ከአርሶ አደሩ ጋር በቅርበት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በመድረኩ የምስራቅ አማራ ቀጠና ዞኖች የግብርና፣ ጤና፣ አደጋ መከላከልና ሌሎች ባለድርሻ አካላት አመራሮችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።      
በተያዘው ዓመት በኢንዱስትሪው የተኪ ምርቶች አቅርቦትን በማሳደግ 5 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማዳን ተችሏል-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 2, 2026 608
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):-በኢንዱስትሪው ዘርፍ በተያዘው ዓመት የሀገር ውስጥ ምርትን በማሳደግና የውጭ ምርቶችን በመተካት አምስት ቢሊዮን ዶላር ምንዛሬ ማዳን መቻሉን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ79.4 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈውና የገጠር ኮሪደር ልማት አካል የሆነውን ዘመናዊውን የሀማሳ ሞዴል መንደር ዛሬ በይፋ መርቀዋል።   መንደሩ የኢትዮጵያ የገጠር ማኅበረሰብን ሕይወት ከባህላዊ አኗኗር ወደ ዘመናዊ ምዕራፍ የሚያሸጋግር መሆኑ ተመላክቷል። ሀማሳ የተሰኘውን ይህንን ዘመናዊ መንደር መርቀው የከፈቱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሲሆኑ፣ ስራው በአገሪቱ የገጠር ማሻሻያ ረገድ አዲስ ምዕራፍ የከፈተ መሆኑን ገልጸዋል። ይህ መንደር በተለይ የገጠሩን ነዋሪ የኑሮ ደረጃና ክብር ከፍ ለማድረግ ታቅዶ የተሰራ ሲሆን፣በአንድ ግቢ ውስጥ ዘመናዊ የንጽህና መጠበቂያዎችን፣ የተደራጀ የቤት እንስሳት ማቆያን፣ በባዮ ጋዝ የሚሰራ የሃይል አቅርቦትን እንዲሁም የተሟላ የጓሮ ግብርናን ያካተተ መሆኑን ጠቁመዋል። የዜጎችን ጤና ለመጠበቅ ንጽህና እና የተመጣጠነ ምግብ ወሳኝ መሆናቸውን የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ እነዚህን መሰረታዊ ነገሮች በማሟላት የሀገሪቱን የብልጽግና ጉዞ ማገዝ እንደሚቻል አስገንዝበዋል።   የዚህ ዘመናዊ መንደር ግንባታ ትልቁ ስኬት፣ሙሉ ወጪው የተሸፈነው በመንግሥት ሳይሆን በአካባቢው አርሶ አደሮች መሆኑ ነው። ባለፈው ዓመት መንግሥት በተለያዩ አካባቢዎች የሞዴል ቤቶችን በመስራት መንገድ ካሳየ በኋላ፣ዘንድሮ ነዋሪዎቹ እራሳቸው ተነሳሽነቱን ወስደው የራሳቸውን መኖሪያዎች መገንባታቸውን ነው ያብራሩት። በዚህም አርሶ አደሮቹ ከመንግሥት የተሰጣቸውን ስልጠናና ሙያዊ እገዛ ብቻ በመጠቀም፣ በገዛ ጓሯቸው አትክልት፣ ፍራፍሬ፣ ማር፣ ዓሳና የዶሮ እርባታን በማስፋፋት የራሳቸውን የኢኮኖሚ አቅም ማሳደግ መቻላቸውን ተናግረዋል። አርሶ አደሮች በራሳቸው ግቢ ውስጥ ይሄንን መሰል ምርታማነት ማምጣት መቻላቸው በኑሮ ላይ የሚፈጠሩ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጫናዎችን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚቀንስ ጠቁመዋል። መንግሥትም ይህንን በአርሶ አደሩ የተጀመረውን አበረታች የልማት ተሞክሮ ወደሌሎች አካባቢዎች ለማስፋፋትና ይበልጥ ለማሳደግ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።   በሌላ በኩል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ‎ዛሬ በጋሞ ዞን የ'ዮ ሆልዲንግ’ የድንጋይ ከሰል ፋብሪካን ጎብኝተዋል። ከጥቂት ዓመታት በፊት ለኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ግብአት የሚሆኑ ከሰሎች ከውጭ ሀገር ይገባ እንደነበር አስታውሰው እስከ 300 ሚሊዮን ዶላር ገደማ የሚደርስ ውጪ እንደሚወጣ አመልክተዋል። አሁን በኢትዮጵያ ከሰል በሀገር ውስጥ እንደሚመረት እና ለኢንዱስትሪ ግብአት እንደሚውል አመልክተዋል። የተለያዩ የከሰል ማምረቻ ፋብሪካዎችም ተመርቀው ወደ አገልግሎት መግባታቸውንና ይህም የሀገር ውስጥ ፍላጎትን ከመሙላት ባለፈ ለውጭ ገበያ የማቅረብ እድል እንደሚፈጥርም ተናግረዋል። በተያዘው ዓመት ኢንዱስትሪው በሀገር ውስጥ የተለያዩ ምርቶችን በማምረት አምስት ቢሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማዳን መቻሉን አመልክተዋል። በአጠቃላይ በኢንዱስትሪው ዘርፍ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አረጋግጠዋል።
በክልሉ በእንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ዘርፍ ያለውን ዕምቅ አቅም ለመጠቀም የተደረጉ ጥረቶች ውጤት አስመዝገበዋል
Jul 2, 2026 139
ሆሳዕና፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ) ፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በእንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ዘርፍ ያለውን ዕምቅ አቅም በመጠቀም የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተደረጉ ጥረቶች ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። የክልሉ ግብርና ቢሮ በእንስሳትና ዓሳ ልማት ዘርፍ የተከናወኑ ስራዎችን የሚገመግም መድረክ በሆሳዕና ከተማ አካሄዷል።   በወቅቱም የቢሮው ምክትል ኃላፊና የእንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ዘርፍ ኃላፊ አቶ እያሱ ተረፈ እንዳሉት፤ በክልሉ በእንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ዘርፍ ያለውን ዕምቅ አቅም በመጠቀም የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በተሰሩ ስራዎች ተስፋ ሰጪ ውጤት ተመዝግቧል፡፡ ለአብነትም የወተት ሀብት ልማት ምርታማነትን ለማሳደግ በተደረገው ጥረት፣ ምርቱ ከቤት ፍጆታ አልፎ አሁን ላይ ስምንት የወተት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪዎችን በማቋቋም የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። ለገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን በጥራትና በብዛት በማምረት ረገድ እየተመዘገቡ የሚገኙ ስኬቶች ይበልጥ እንዲጠናከሩ በትኩረት እንደሚሰራም ገልጸዋል። በቢሮው የእንስሳትና ዓሳ ዘርፍ ልማት ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ሙሉጌታ ተስፋዬ በበኩላቸው፤ በክልሉ የእንስሳትና ዓሳ ሀብት ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያስችሉ ስራዎች በትኩረት እየተሰሩ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   በእንስሳት ዝርያ ማሻሻል፣ በእንስሳት ጤና አጠባበቅ፣ በመኖ ልማት፣ በማሽነሪና በቴክኖሎጂ ሽግግር አርሶ አደሩን በህብረት ስራ ማህበራት በማደራጀት በተቀናጀ መልኩ ተጠቃሚ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በዚህም በክልሉ በዘርፉ የተሰማሩ 57 የህብረት ስራ ማህበራትን እና ከ219 ሺህ በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን በቀጥታ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። በመድረኩ ከተሳተፉት መካከል የምስራቅ ጉራጌ ዞን ዋልታ የገበሬዎች ህብረት ስራ ዩኒየን ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ ያሲን ሀሰን፤ ዩኒየኑ በተደረገለት ድጋፍ በዶሮ እርባታና በእንስሳት መኖ ማቀነባበር ዘርፍ ተሰማርቶ ተጨማሪ ገቢ እያገኘ መሆኑን ገልጸዋል። ዘርፉ ያለውን አቅም ለማጠናከር የተጀመረው ጥረት ገበያን ለማረጋጋት ያስቻለ ምርት እያስገኘ መሆኑን አንስተው፣ በዚህ ዓመት ብቻ ከ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ እንቁላል ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚነታቸው እንዲጨምር መደረጉን ጠቁመዋል። በተሰማሩበት የእንስሳት እርባታ ዘርፍ ውጤታማ እንዲሆኑ በዝርያ ማሻሻል ረገድ በተደረገላቸው ድጋፍ ስኬታማ እየሆኑ ስለመምጣታቸው የተናገሩት ደግሞ በሀዲያ ዞን የሌሞ ወረዳ ነዋሪዋ ወይዘሮ ዘነበች ጋርከቦ ናቸው።   በቀን እስከ 50 ሊትር ወተት ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ጠቁመው፣ በዚህም ልጆቻቸውን ከማስተማር ባለፈ ለነገ የሚሆናቸውን ተጨማሪ ሀብት እንዲያፈሩ ምቹ ሁኔታ እንደተፈጠረላቸው አስረድተዋል። በዚህ የምክክር መድረክ መርሐ ግብር ላይ የክልልና የዞኖች የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ የህብረት ስራ ማህበራት፣ ዩኒየኖችና አርሶ አደሮች ተሳትፈዋል።  
በምዕራብ ጎንደር ዞን በመኸር ወቅት ከ400 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሜካናይዜሽን ይለማል
Jul 2, 2026 152
ገንዳውኃ፣ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- በምዕራብ ጎንደር ዞን በመጪው መኸር ከ400 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሜካናይዜሽን እንደሚለማ የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። የምዕራብ ጎንደር ዞን ከፍተኛ አመራሮች፣ የግብርና ባለሙያዎችና አልሚ ባለሀብቶች የተጀመረውን የሜካናይዜሽን እርሻ እንቅስቃሴ ለመገምገምና ለማበረታታት በመተማ ወረዳ የመስክ ምልከታ አካሂደዋል። በጉብኝቱ ወቅትም የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ እንደገለጹት፤ ዞኑ ገበያ ተኮር የግብርና ምርቶች የሚመረቱበት መሆኑን ገልፀዋል። በዚህም ሰሊጥ፣ አኩሪ አተር፣ ጥጥ፣ ቦሎቄ፣ ማሽላና ሌሎች የሰብል አይነቶችን በዓይነትና በብዛት በማምረት፣ በወጪ ንግድ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማስፋት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። ምርታማነትን ለማሳደግም አልሚ ባለሀብቶችና አርሶ አደሮች የተሻሻለ ዘርና ማዳበሪያን ከመጠቀም ባሻገር፣ በምርት ማምረትና አሰባሰብ ወቅት ዘመናዊ የግብርና አሰራርን ተግባራዊ እንዲያደርጉ አስገንዝበዋል። የዞኑ መስተዳድርም ከህዝቡ ጋር በመቀናጀት ሰላሙን በማስጠበቅ፣ የነዳጅና የግብርና ግብዓት አቅርቦትን በማሻሻል ረገድ እያደረገ ያለውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊና ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አንዳርጌ ጌጡ በበኩላቸው፤ ዞኑ ሰፊ መሬት፣ ተስማሚ ስነ ምህዳርና የአየር ጸባይ የታደለ በመሆኑ ለእርሻ ኢንቨስትመንት ተመራጭ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም በአጠቃላይ ከ529 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር በመሸፈን የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ፣ ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለውጭ ገበያ የሚሆኑ ምርቶችን በስፋት ለማምረት እየተሰራ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከሚለማው መሬት ውስጥ ከ400 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነውን በሜካናይዜሽንና በኩታ ገጠም ለማልማት ታቅዶ፣ እስካሁን 250 ሺህ ሄክታሩን በዘር መሸፈን መቻሉን ተናግረዋል። ይህም ምርታማነትን በማሳደግ፣ የምርት ብክነትን በመቀነስና ጥራት ያለው ምርትን በማምረት የወጪ ንግዱን ለማሳላጥ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። በመተማ ወረዳ ኮኪት አካባቢ በግብርና ኢንቨስትመንት ላይ የተሰማሩት አቶ ሳኒ እንድሪስ በበኩላቸው፤ በሜካናይዜሽን በመታገዝ የግብርና ልማት ስራቸውን እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ያወጡት የነበረውን ወጪና ያባክኑት የነበረውን ጉልበት ለመቀነስ እንደቻሉ አስረድተዋል። በዘንድሮው የሰብል ልማት የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎችን በስፋት ለመጠቀም መዘጋጀታቸውን የገለጹት ደግሞ በወረዳው በግብርና ስራ ላይ የተሰማሩት ባለሀብትና አርሶ አደር አቶ ደምስ ሽታ ናቸው። ከመንግስት በኩል እየተደረገ ያለው የጸጥታ ጥበቃና የቴክኒክ ድጋፍ የሚበረታታ መሆኑን ጠቁመው፣ ይህ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥልም አሳስበዋል። በመተማ ወረዳ በኮኪት ከተማና አካባቢዋ የተጀመረውን የተቀናጀ የሜካናይዜሽን እርሻ ንቅናቄ ወደ ሌሎች ወረዳዎች ለማስፋት እየተሰራ መሆኑንም ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።  
የሀገር ውስጥ ምርትን በራስ አቅም ማሳደግ የሉዓላዊነታችን መሰረት ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 2, 2026 231
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ)፡- የሀገር ውስጥ ምርትን በራስ አቅም ማሳደግ የኢኮኖሚ ነጻነታችን እና የሉዓላዊነታችን መሰረት ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትሥሥር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ በጋሞ ዞን የሚገኘውን እና ነሐሴ 2017 ዓ.ም ላይ ሥራ የጀመረውን 'ዮ ሆልዲንግ’ የድንጋይ ከሰል ፋብሪካ መጎብኘታቸውን አስታውቀዋል።   ፋብሪካው የኢንዱስትሪዎቻችንን ፍላጎት በሀገር ውስጥ በመተካት ከውጭ የሚገባ ምርትን ያስቀረ መሆኑን ገልጸዋል። ለአካባቢው ነዋሪዎችም የሥራ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል በመልዕክታቸው።   የሀገር ውስጥ ምርትን በራስ አቅም ማሳደግ የኢኮኖሚ ነጻነታችን እና የሉዓላዊነታችን መሰረት ነው ሲሉም አስገንዝበዋል። ‎የሀገራችንን የተፈጥሮ ሀብት በጠንካራ ስራ በሀገር ውስጥ በማልማት የኢኮኖሚ ልዕልናችንን የምናረጋግጥበት ጉዞ ተጠናክሮ ይቀጥላልም ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
በግብርናው ዘርፍ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮች መዘርጋታቸው ከተረጂነት ለመውጣት እየተደረገ ያለውን ጥረት በከፍተኛ ሁኔታ ያግዛል 
Jul 2, 2026 185
ጅማ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):-ባለፉት ዓመታት በግብርናው ዘርፍ በቴክኖሎጂ የታገዙ አሰራሮች መዘርጋታቸው ከተረጂነት ለመውጣት እየተደረገ ያለውን ጥረት በከፍተኛ ሁኔታ ያግዘዋል ሲሉ የጅማ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ። ምሁራኑ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ቴክኖሎጂና ግብዓት በወቅቱ የተሟላለት የግብርና ስራ ምርታማ በመሆኑም የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማሳደግ ከተረጂነት ለመውጣት እየተደረገ ያለውን ጥረት ያፋጥናል። በጅማ ዩኒቨርሲቲ የግብርና ምጣኔ ባለሙያ እና ተመራማሪ አደባ ገመቹ (ዶ/ር)፤ ግብርናው በቴክኖሎጂ የታገዘ በመሆኑ ምርታማነትን እያሳደገ መጥቷል ብለዋል።   ባለፉት ዓመታት መንግሥት በሁሉም እንቅስቃሴዎቹ የባለሙያዎችን እና የአርሶ አደሩን ግንዛቤ ለማሳደግ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ መስራቱንም አስታውሰዋል። በዲጂታል ግብርና ትግበራ አርሶ አደሩ መሬት ለማዘጋጀትና ዘር ለመዝራት መጠቀም ያለበትን ትክክለኛ ጊዜን ጨምሮ፣ ሌሎች ተያያዥ መረጃዎችን እንዲያገኝ መደረጉ የምርታማነት ዕድገት ጥረቱን ወደ ተጨባጭ ውጤት እየቀየረው መሆኑን ገልጸዋል። ለአርሶ አደሮች የምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት በበቂ ሁኔታ እንዲደርስ መደረጉም ለተገኘው ውጤት ሌላኛው ምክንያት መሆኑን አክለው ገልጸዋል። በዚህም ግብርናውን ከዝናብ ጠባቂነት በማላቀቅ በመስኖና በሌሎች አማራጮች በዓመት ሁለትና ከዚያ በላይ ማልማት፣ የአርሶ አደሩን ሕይወት ከማሻሻል ባለፈ ከተረጂነት ለመውጣት እንደሚቻል አስረድተዋል። ከዚህ ባለፈም የገበያ ትስስርን በመፍጠር፤ የኮንትራት እርሻን ጨምሮ ሌሎች አማራጮችን በመጠቀም በቀጥታ ከአርሶ አደሩ ምርት የሚረከቡ ተቋማትና ፋብሪካዎች መፈጠራቸው በዘርፉ ትልቅ ለውጥ ማምጣቱን ጠቅሰዋል። በዩኒቨርሲቲው የግብርናና እንስሳት ሕክምና ኮሌጅ ዲን፣ የአፈር ልማት፣ የሰብል እንክብካቤና ንጥረ-ነገር ባለሙያ ሰለሞን ቱሉ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ባለፉት ዓመታት ለግብርናው ዘርፍ በተሰጠው ትኩረት ምርታማነትን በማላቅ ረገድ ተጨባጭ ለውጥ መመዝገቡን ገልጸዋል።   በዚህም የፍራፍሬና የቅባት እህሎች በስፋት ከመመረታቸውም በላይ ምርቶቹን የሚያቀነባብሩ ፋብሪካዎች መቋቋማቸውን ጠቁመዋል። በቴክኖሎጂ በመታገዝ ምርትን በአግባቡ መሰብሰብ በመቻሉም የብክነት መጠን ቀንሶ ምርታማነት መጨመር መቻሉንም አክለዋል። እንዲሁም መንግሥት ዘመናዊ የግብዓት ማቆያና ማከማቻ ሥፍራዎችን አዘጋጅቶ ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ማድረጉና ሰፊ ግንዛቤ መፍጠሩ በዘርፉ የታየ ሌላኛው ትልቅ የለውጥ ምዕራፍ መሆኑንም አስረድተዋል። ከዚህም ባሻገር የአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ከሚያስከትለው ችግር በመከላከል ረገድ ለግብርናው ዘርፍ በጎ ሁኔታ መፍጠሩንም አመልክተዋል። ወጣቶችን በግብርና በማሳተፍ፣ የአፈር ጥበቃ ሥራዎችን በማጎልበትና የምርጥ ዘር አቅርቦትን በማሳለጥ ረገድ የተሰጠው ልዩ ትኩረት ለስኬቱ አጋዥ መሆኑንም አብራርተዋል። መሰል ሥራዎች ከተረጂነት ለመውጣት የሚደረገውን ጥረት እያገዙ መሆናቸውን ጠቁመው የሚፈለገው ግብ ላይ ለመድረስ ሁላችንም ልንረባረብ ይገባል ብለዋል።
የንግድ ባዛሩ ለአምራቾች ምርትን ከማስተዋወቅ ባለፈ የገበያ ትስስር እየፈጠረ ነው
Jul 2, 2026 149
ወልቂጤ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):-በወልቂጤ ከተማ የተከፈተው የንግድ ባዛርና አውደ ርዕይ ምርቶቻቸውን ከማስተዋወቅና ከመሸጥ ባለፈ የገበያ ትስስር ለመፍጠር እያገዛቸው መሆኑን አምራቾችና ኢንተርፕራይዞች ገለጹ። ለሦስት ቀናት በሚካሄደው አውደ ርዕይ እና ባዛር ላይ ከ120 በላይ አምራቾች የግብርና፣ የኢንዱስትሪ እና የእደ ጥበብ ምርቶችን ይዘው ቀርበዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ አምራቾችና ኢንተርፕራይዞች እንዳሉት አውደ ርዕዩና ባዛሩ ምርቶቻቸውን ለማስተዋወቅና ለመሸጥ እንዲሁም ለቀጣይ የገበያ ትስስር ለመፍጠር እያገዛቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡   ከባዛሩ እና አውደርዕዩ ተሳታፊዎች መካከል የዳሪም ዱቄት ፋብሪካ የሰው ሃብትና ንብረት አስተዳደር ማናጀር አቶ ወንድምአገኝ ታሪኩ፣ ጥራት ያላቸውን ምርቶች በተመጣጣኝ ዋጋ ይዘው መቅረባቸውን ገልጸዋል። ቀደም ባሉት ጊዜያት በተለያዩ አካባቢዎች በተዘጋጁ ባዛርና አውደ ርዕይ ላይ ሲሳተፉ መቆየታቸውን ገልጸው፣ ይህም የገበያ ዕድልን ለማስፋትና ደንበኛ ለማፍራት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። ከወልቂጤ ማረሚያ ተቋም የተለያዩ የእደ ጥበብ ውጤቶች ይዘው በባዛሩ ላይ የተሳተፉት አቶ አብድልከሪም ጀማል በበኩላቸው፤ በባዛሩ የተፈጠረላቸው የገበያ ዕድል ምርቶቻቸውን በመሸጥ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ማረሚያ ተቋሙ ታራሚዎችን በስነ ምግባር ከማነጽ ባለፈ የተለያየ ሙያ ባለቤት እንዳደረጋቸው ገልጸው፣ በኢንተርፕራይዝ በማደራጀት ለብዙዎች የሥራ ዕድል ፈጥሮ ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን ተናግረዋል።   የንግድ ባዘሩና አውደ ርዕዩ አምራቹን ከሸማቹ ማህበረሰብ ጋር በማገናኘት ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን የገለጹት ደግሞ የፍኸር ጨርቃጨርቅ ማኑፋክቸሪንግ ማህበር ሰብሳቢ ወይዘሮ ዚኪራ ሙራድ ናቸው። ኢንተርፕራይዞች እርስ በርስ ልምድ ከመለዋወጥ ባለፈ የገበያ ዕድል ለማግኘት ማስቻሉን ገልጸው፣ በባዛሩ ከሌሎች ጋር የገበያ ትስስር እየፈጠሩ መሆኑንም ተናግረዋል። በባዛሩ ላይ ግብይት ሲፈጽሙ የነበሩት የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሪት አሰለፈች አህመድ በበኩላቸው፤ የእደ ጥበብ ውጤቶችን ጨምሮ የተለያዩ ቁሶችን በተመጣጣኝ ዋጋ መሸመታቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለያዩ ጊዜያት የሚዘጋጁ ባዛርና አውደርዕዮች ሸማቹን ከአምራቹ ጋር ስለሚያገናኙ ሁለቱንም ተጠቃሚ ያደርጋል ያሉት ነዋሪዋ፣ በቀጣይም ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል።   በወልቂጤ ከተማ ለሦስት ቀናት በተዘጋጀው የንግድ ባዛርና አውደ ርዕይ ከ120 በላይ አምራቾች የግብርና፣ የኢንዱስትሪ እና የእደ ጥበብ ውጤቶችን ይዘው ቀርበዋል ያሉት ደግሞ የጉራጌ ዞን ሥራ ዕድል ፈጠራ እና ኢንተርፕራይዝ መምሪያ ሃላፊ አቶ ሙራድ ያሲን ናቸው። እሳቸው እንዳሉት ባዛር እና አውደርዕዩ የገበያ ትስስር ለመፍጠር፣ ልምድ ለመለዋወጥ እና የእርስ በእርስ ግንኙነትን ለማጠናከር ያለመ ነው።
በሐረሪ ክልል በቱሪዝም ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ቅርሶችን በመታደግ የሐረርን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻነት እያጎለበቱ ነው
Jul 2, 2026 148
ሐረር፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- በሐረሪ ክልል በቱሪዝም ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ቅርሶችን በመታደግ የሐረርን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻነት ማጎልበቱን የክልሉ ቱሪዝም ኮሚሽን ገለጸ። መንግሥት ያዘጋጀው የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ-ግብር ከለያቸው አምስት ቁልፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ምሰሶዎች መካከል ቱሪዝም አንዱ ነው። ከዚህ ቀደም ዘርፉ በበቂ ሁኔታ ሳይለማና የገቢ ምንጭነቱ ሳይጎለብት በመቆየቱ፣ አሁን ላይ ሀገራዊ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማሳደግ እና የሥራ ዕድል ለመፍጠር እንደ ዋና ሞተር ተለይቶ እየተሰራበት ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል በሰጡት ማብራሪያም በዘርፉ ልማት የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው፤ የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በማሳያ አስቀምጠዋል።   የጥንት ውበታቸውን ከዘመናዊ ገጽታ ጋር በማሰናሰል የቱሪዝም መዳረሻ እንዲሆኑ በለውጡ መንግሥት እንደ አዲስ ከተገነቡና ከተሻሻሉ የኢትዮጵያ ከተሞች መካከል ጥንታዊቷና ታሪካዊቷ የሐረር ከተማ ቀዳሚዋ ነች። የሐረር ጀጎል ግንብና በውስጡ የሚገኙት ጥንታዊ፣ ሃይማኖታዊና ታሪካዊ ቅርሶች ከኢትዮጵያ አልፎ የዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ሀብት መሆናቸው ይታወቃል። በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ እየተተገበረ ያለው የኮሪደር ልማትና የቅርሶች እድሳት ስራ፣ የታሪካዊቷን ሐረር ከተማ የቱሪዝም ዘርፍ ይበልጥ በማነቃቃት ለአካባቢያዊና ሀገራዊ ኢኮኖሚው አዲስ አቅም እየፈጠረ ይገኛል። የክልሉ የቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሚ አብዱልዋሲ እንደገለጹት፣ በክልሉ ያለውን የቱሪዝም ዘርፍ ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገርና እምቅ አቅሙን ለመጠቀም መጠነ-ሰፊ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል።   የቱሪዝም ዘርፉን ለማጎልበት የተከናወኑት ተግባራትም ለአደጋ ተጋርጠው የነበሩ ቅርሶች እንዲለሙና ይዘታቸውን ጠብቀው ለትውልድ እንዲተላለፉ ማስቻላቸውን ኮሚሽነሩ ገልጸው፤ ይህም ለዘርፉ መነቃቃት ትልቅ አቅም ፈጥሯል። በዘርፉ በተሰጠው ትኩረት የቱሪዝም መስህቦችን በማልማት፣ የጎብኚዎችን ቆይታ በማራዘምና ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ አቅም በማሳደግ ረገድ የተሻሉ ተግባራት የተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮ ዓመት ክልሉን የጎበኙ የውጭ ቱሪስቶች ቁጥር ካለፈው ዓመት የ47 በመቶ ብልጫ ማሳየቱን የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ ይህም መሠረተ-ልማቶች ሲሟሉ የቱሪዝም ዘርፉ የኢኮኖሚው ዋነኛ ምሰሶ እንደሚሆን አመላካች ነው ሲሉ ተናግረዋል። እንደ አቶ ሳሚ ገለጻ፣ የቱሪዝም ዘርፉን ለማጎልበት የተከናወኑት ተግባራት ከውጭ ሀገር ቱሪስቶች ባሻገር የሀገር ውስጥ ጎብኚዎች፣ የማኅበራዊ ሚዲያ አንቂዎችና ሌሎች አካላት ሐረርን እንዲጎበኙና ውበቷን ለዓለም እንዲያስተዋውቁ ሰፊ ዕድል ፈጥሯል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በተያዘው ክረምት በ100 ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ በኩታ ገጠም ይተከላል
Jul 2, 2026 133
ደብረ ማርቆስ ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):-በምስራቅ ጎጃም ዞን በተያዘው ክረምት በ100 ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ በኩታ ገጠም እንደሚተከል የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የአትክልትና ፍራፍሬ ባለሙያ አቶ ተሾመ በላይ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለቡና ልማት ስራ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በዞኑ በያዝነው ክረምት በቡና ከሚለማው አጠቃላይ ከ320 ሄክታር መሬት ውስጥ ከ100 ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት በኩታ ገጠም የሚለማ መሆኑን ገልጸዋል። በአጠቃላይ በበጋው ወቅት ከተዘጋጀው ከ916 ሺህ በላይ የቡና ችግኝ ውስጥም ከ330 ሺህ በላይ የሚሆነው ለኩታ ገጠም ልማት እንደሚውል ተናግረዋል። የቡና ኩታ ገጠም ልማቱ የሚካሄደውም ተስማሚ ስነ ምህዳርና የአየር ንብረት ባላቸው በደብረ ኤሊያስ፣ በማቻከልና ጎዛምን ወረዳዎች መሆኑን አመላክተዋል።   በዞኑ በሚካሄደው የቡና ልማትም ከ690 በላይ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ እንደሚገኙ አስረድተዋል። በዞኑ የጎዛምን ወረዳ የሊባኖስ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ክብረት በዛበህ ፤ በተያዘው ዓመት ቡናን በኩታ ገጠም መትከል መጀመራቸውን ነው የሚናገሩት። ከዚህ በፊት ቡናን በጓሯቸው በማልማት ለቤት ውስጥ ፍጆታ ይጠቀሙ እንደነበር አስታውሰው በአሁኑ ወቅም ከግማሽ ሄክታር በላይ የሚሆን መሬት ላይ ቡናን በኩታገጠም በማልማት ለገበያ ለማቅረብ እየሰራሁ ነው ብለዋል። የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መንግስቱ ክፍሌ በበኩላቸው እንደሌሎች ሰብሎች ቡናን በኩታ ገጠም ለማልማት ከግማሽ ሄክታር በላይ መሬት በማዘጋጀት ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም የማሳ ዝግጅት በማጠናቀቅ በጋራ የሚተከልበትን ቀን በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል።
የሸገር ከተማ አስተዳደር በበጀት ዓመቱ 37 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ ሰብስቧል
Jul 2, 2026 129
ሸገር፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- የሸገር ከተማ አስተዳደር በበጀት ዓመቱ 37 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰቡን የከተማው የገቢዎች ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የሸገር ከተማ አስተዳደር በኦሮሚያ ክልል ልዩ ልዩ ወረዳዎችንና ከተሞችን በማጣመር በቅርብ ዓመታት የተመሰረተ ሰፊና አዲስ ከተማ ነው። ከተማው ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ ግዙፍ የኮሪደር ልማት፣ የመሰረተ ልማት ዝርጋታና የከተማ ውበት ፕሮጀክቶችን በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። እነዚህን ሰፊ የልማት ፍላጎቶች በራስ አቅም ለመደገፍና የከተማውን ሁለንተናዊ እድገት ለማፋጠን የውስጥ ገቢ አቅምን ማሳደግ ቀዳሚው የቤት ስራ ሆኖ ቆይቷል። ጽሕፈት ቤቱ በበጀት ዓመቱ የሰበሰበው ይህ ከፍተኛ ገቢ፥ የከተማዋን የልማት ፕሮጀክቶች በራስ አቅም ለመሸፈንና የህዝብን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ እየተደረገ ላለው ጥረት ትልቅ ስኬት እንደሆነ ይታመናል። የከተማ አስተዳደሩ ገቢዎች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መልካሙ አምባው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተማ አስተዳደሩ በበጀት ዓመቱ በአጠቃላይ 39 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ነበር። በበጀት ዓመቱም ከተለያዩ የገቢ ምንጮች 37 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ገቢ በመሰብሰብ የዕቅዱን 95 በመቶ ማሳካት መቻሉን ተናግረዋል። የገቢ አሰባሰብ ሂደቱ ስኬታማ የሆነው የታክስ አሰባሰብ ሥርዓትን ማሻሻልና ለዘርፉ ልዩ ትኩረት መሰጠቱ እንዲሁም ለግብር ከፋዮች ቀጣይነት ያለው ግንዛቤ መፍጠር በመቻሉ ነው ብለዋል። ከዚህም ባለፈ ሕጋዊ ደረሰኝ የመቁረጥ ልምድን ማሳደግ፣ ቴክኖሎጂን በማስፋት ግብር ከፋዮች ግብራቸውን ግልጽና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ እንዲከፍሉ ምቹ ሁኔታ በመፈጠሩ መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ከ400 በላይ ከፍተኛ ግብር ከፋዮች ባሉበት ሆነው በዲጂታል መንገድ የሚጠበቅባቸውን ግብር እና ክፍያዎች መፈጸም መቻላቸውን ገልጸዋል። ይህንን የዲጂታላይዜሽን ሥርዓት ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግና ወደ ሙሉ ሥራ ለማስገባት ለባለሙያዎች የአቅም ግንባታ ሥልጠና እየተሰጠ መሆኑን ኃላፊው አብራርተዋል። የዘርፉን አዋጆችና መመሪያዎች በመከተል እንደ ታክስ ስወራ ያሉ ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴዎችን ለመቆጣጠር የተቀናጀ ኮሚቴ ተዋቅሮ ክትትል እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ሕገ-ወጥነትን ለመከላከል በተሰሩ ሥራዎችም በበጀት ዓመቱ በሕገ-ወጥ መንገድ ሲንቀሳቀሱ የተገኙ ስድስት ነጋዴዎች ላይ ሕጋዊ እርምጃ መወሰዱን አስታውሰዋል። በተጨማሪም ሕጋዊ ደረሰኝ ባለመቁረጣቸው ምክንያት በ240 ነጋዴዎች ላይ የገንዘብና አስተዳደራዊ ቅጣት መጣሉን ገልጸው፤ በቀጣይም የዲጂታል አሠራርን በማዘመንና በደንበኞች ዘንድ ግንዛቤ በመፍጠር ላይ ትኩረት ተደርጎ እንደሚሠራ ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ የባሕር በር ብታገኝ የሚጠቀም እንጂ የሚጎዳ ሀገር እንደሌለ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ተገንዝቧል
Jul 2, 2026 153
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ታሪካዊ፣ ሕጋዊና መልክዓ ምድራዊ መሰረት ያለው የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው ወሳኝ አጀንዳ መሆኑን ምሁራን ገለጹ። ምሁራኑ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት መብት ለማስከበር የሚከናወኑ ተግባራት ሳይንሳዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገድን የተከተሉ ናቸው። የሀገር ውስጥ ባንዳና የውጭ ባዕዳን ኃይሎች ኢትዮጵያ ላለፉት ሦስት አሥርት ዓመታት በላይ ከተፈጥሯዊና ታሪካዊ የባሕር በር ባለቤትነት ተነጥላ እንድትቆይ ማድረጋቸው ይታወሳል። ከሀገራዊ ለውጡ ማግስት የመደመር መንግሥት የትውልድን የተዳፈነ ጉዳይ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም አጀንዳ በማድረግ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ወደ ዓለም አቀፍ ቅቡልነት አሸጋግሯል። በኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማሲና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር እንዳለ ንጉሴ፤ የባሕር በር ባለቤትነት የሀገርን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት የሚያረጋግጥ የብሔራዊ ጥቅም ማዕከል ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከታሪካዊ፣ መልክዓ ምድራዊና ሕጋዊ መሠረት ባሻገር ብሔራዊ ጥቅምንና አዳጊ የሀገርና የዜጋ ፍላጎትን ማዕከል ያደረገ ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም ሕዝብና መንግሥት የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ምላሽ ለማስገኘት በውጤታማ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ በተደገፈ ሳይንሳዊ የዲፕሎማሲ መርህ ወደ ዓለም አቀፍ ቅቡልነት ማሸጋገራቸውን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነትም ሀገርን ከተፈጥሯዊ ማንነቷ በማስታረቅ ቀጣናዊ ሰላምና ደኅንነትን ዕድገትና ብልፅግናን የሚያረጋግጥ ወሳኝ የትብብር ዕድል መሆኑን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የባሕር በር ብታገኝ የሚጠቀም እንጂ የሚጎዳ ሀገር እንደሌለ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ መገንዘቡንም ነው ያነሱት። ኢትዮጵያ ጫናን በመቋቋም በዲፕሎማሲ ስኬት ሕዳሴ ግድብን ዕውን በማድረግ ቀጣናዊ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ትስስርን በመፍጠር ተምሳሌታዊነቷን በተግባር እያስመሰከረች እንደምትገኝም ገልጸዋል። ኢትዮጵያውያንም ሕዳሴን በትብብር እንዳሳኩት ሁሉ፤ አንድነትን በማጠናከር የትውልድ ጥያቄ የሆነውን የባሕር በር ባለቤትነት ለማስከበር በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ ገልጸዋል። በዩኒቲ ዩኒቨርሲቲ የሥነ-አመራርና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህሩ ጌትዬ ትርፌ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የባህር በር ያጣችው በውጭ ታሪካዊ ጠላቶችና በውስጥ ባንዳዎች ጥምር ሴራ ነው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ከባሕር በር ባለቤትነቷ እንድትርቅ የተፈጸመባት ኢ-ፍትሐዊ በደል ቀጣናውን የሽብርተኞች መፈንጫ በማድረግ የጋራ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያቀጨጨ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ብሔራዊ ጥቅምን የማስከበር የህልውና ጉዳይ ሆኖ መቅረቡም ቅቡልነት ያለው አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል።
የእርሻ ስራን በግብርና ባለሙያ በመታገዝ በማከናወናችን ምርታማነታችን አድጓል-የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች
Jul 2, 2026 114
ወልቂጤ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- የመኸር ወቅት የእርሻ ስራን በግብርና ባለሙያዎች በመታገዝ እያከናወኑ በመሆኑ ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱን የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። የዞኑ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በግብርና ባለሙያዎች እየተደረገላቸው ያለው ድጋፍ የተቀናጀ የግብርና ስነ-ዘዴን በመጠቀም በእንስሳት እርባታም ጭምር ውጤታማ ሆነዋል። የእርሻ ስራን በግብርና ባለሙያዎች በመታገዝ እያከናወኑ በመሆኑ ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱንም አርሶ አደሮቹ ገልጸዋል። የአበሽጌ ወረዳ ነዋሪው አርሶ አደር ሰብስቤ ወልደሃዋርያት፤ አሁን ላይ ለዘር ምቹ ወቅት በመሆኑ በግብርና ባለሙያዎች ታግዘው የግብርና ልማት ሥራቸውን እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል።   በዚህም እስካሁን ሁለት ሄክታር መሬታቸውን በበቆሎ ዘር መሸፈናቸውንና አንድ ሄክታሩን ደግሞ በጤፍ ለመሸፈን መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። በዞኑ የጌታ ወረዳ አርሶ አደር ጀማል ሟናጋ በበኩላቸው፤ ድንችን በአንድ ሄክታር መሬት ላይ ተክለው በመንከባከባቸው ለምግብ ፍጆታ የሚውል ምርት ከማምረት ባለፈ ለገበያ ጭምር በማውጣት ትርፋማ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ቀሪ አንድ ሄክታር ከግማሽ መሬታቸውን አርሰው በማለስለስ ሰብል ለመዝራት መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል። የሚደረግላቸው ሙያዊ ድጋፍ ምርታማነታቸውን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የተሳካ ስራ እንዲሰሩ ምክንያት እንደሆነ የገለፁት ደግሞ አርሶ አደር ገብሬ ዛጋ ናቸው። የተቀናጀ የግብርና አሰራርን በመከተል የተለያዩ ሰብሎችን በማልማትና እንስሳትን በማርባት ተግባር ላይ መሰማራታቸው የተሻለ ኑሮ እንዲመሩ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። ዘንድሮም ካላቸው የእርሻ መሬት ላይ አንድ ሄክታር መሬት በገብስ ለመሸፈን መዘጋጀታቸውን ጠቅሰው ለዚህም የአፈር ማዳበሪያ እና ምርጥ ዘር እንደቀረበላቸው ተናግረዋል።   የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ፤ በዞኑ በተያዘው መኸር ከ43 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበቆሎ ዘር መሸፈኑን ተናግረዋል። በመኸር እርሻ 180 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት መታረሱን ገልፀው እስካሁን 160 ሺህ የሚጠጋ ማሳ መልማቱን አስረድተዋል። የግብርና ሜካናይዜሽንን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማላቅ እየተሰራ ያለው ስራ የዘርፉን ውጤታማነት እያሳደገው መሆኑንም አቶ አበራ አመልክተዋል።
በደቡብ ወሎ ዞን ከ 46 ሺህ በላይ ለሚሆኑ አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ተሰጠ 
Jul 2, 2026 146
ደሴ ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):- በደቡብ ወሎ ዞን ከ46 ሺህ በላይ ለሚሆኑ አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ መስጠቱን የዞኑ መሬት መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የገጠር መሬት አስተዳደር ቡድን መሪ አቶ ምሳው አክቤ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በዞኑ የሚገኙ አርሶ አደሮችን ዘላቂ የመሬት ባለቤትነት ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ውጤታማ ናቸው። ከዚህ ውስጥም በበጀት ዓመቱ ለ46 ሺህ 311 አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ በመስጠት መሬታቸውን በዘላቂነት አልምተው እንዲጠቀሙ ተደርጓል ነው ያሉት።   የይዞታ ካርታው የአርሶ አደሩን ይዞታ በሳይንሳዊ መንገድ በመለካትና ማረጋገጫ በመስጠት የብድርና ሌሎች አገልግሎቶችን ለማግኘት ሰፊ እድል የፈጠረ እንደሆነም አስረድተዋል። በተጨማሪም አርሶ አደሩ በይዞታው በሚያገኘው የብድር አገልግሎት የግብርና ስራውን ለማዘመን የሚያስችለው ከመሆኑ ባለፈ ሌሎች የገቢ ማስገኛ ስራዎች ላይ እንዲሰማራ የሚያደርግ ነው ብለዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ ብቻ አራት ሺህ 693 አርሶ አደሮች ከ127 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉን አስረድተዋል። በዞኑ ደሴ ዙሪያ ወረዳ የ032 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መሀመድ ሰይድ ፣የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ማግኘቴ መሬቱን በተሻለ መንገድ ለማልማትና ተጨማሪ ሀብት ለማፍራት አስችሎኛል ብለዋል። ቀደም ሲል የነበረው ይዞታ ትክክለኛ ልኬት ያልነበረው በመሆኑ ከሌላ ባለመብት ጋር የመገፋፋት ሁኔታ ይፈጠር እንደነበር አስታውሰው ፣ አሁን ችግሩ ሙሉ ለሙሉ መፈታቱን ገልጸዋል። "የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታው ወሰንና ልኬትን በትክክል ያስቀመጠ በመሆኑ የመሬታችንን ዘላቂ ዋስትና ያረጋገጠ ነው" ያሉት ደግሞ የወረኢሉ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ጀማል ዋሴ ናቸው። ይህም ይገባኛል በሚል ይፈጠሩ የነበሩ ግጭቶችንና አለመግባባቶችን በማስቀረቱ ምርታማነታችን ለመጨመር ያግዘናል ነው ያሉት። በደቡብ ወሎ ዞን ባለፈው በጀት ዓመት ከ61 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች የ2ኛ ደረጃ የመሬት ማረጋገጫ ካርታ መስጠት መቻሉን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
ባለፉት የለውጥ ዓመታት በቱሪዝም ዘርፍ በተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት ታይቷል 
Jul 2, 2026 198
ሮቤ ፤ ሰኔ 25/2018 (ኢዜአ):-በኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በቱሪዝም ልማት ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭና አበረታች ውጤት ማስመዝገባቸውን የዘርፉ ምሁራን አስታወቁ። ​ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል በሰጡት ማብራሪያ በዘርፉ ልማት የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በማሳያ አስቀምጠዋል። በተለይም በባሌ አካባቢ የሚገኙ የሶፍ ኡመር ዋሻ፣ ድሬ ሼህ ሁሴን፣ ባሌ ተራሮችን ጨምሮ ሌሎች የገበታ ለሀገር ፕሮጀክቶች ግንባታ፣ የከተሞች ኮሪደር ልማትና የቅርሶች እድሳት ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ትልቅ አቅም መሆናቸውን አብራርተዋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የቱሪዝም ዘርፍ መምህራንና ተመራማሪዎች እንዳሉት፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የባሌ ዞንን እምቅ የቱሪዝም አቅም በልዩ ሁኔታ የገለጹበት መንገድ ለዘርፉ መነቃቃት ከፍተኛ መሠረት የሚጥል መሆኑን ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው መምህርና የዘርፉ ተመራማሪ ስንታየሁ አይናለም(ዶ/ር) እንዳሉት፤ የባሌ ዞን የተለያዩ ሥነ-ምህዳሮች በአንድ ላይ የሚገኙበት መሆኑ ለቱሪዝም ዘርፉ ትልቅ አቅም መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይም መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት የቱሪዝም መስህቦችን በማልማት፣ የጎብኚዎችን ቆይታ በማራዘምና ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ በማሳደግ ረገድ የተሻሉ ተግባራት የተከናወኑበት መሆኑን ምሁሩ ገልጸዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የቱሪዝም ልማት ኢኒሼቲቮች አጠቃላይ የቱሪዝም ዘርፉን እያነቃቁት መሆኑን የጠቀሱት ተመራማሪው፤ ዩኒቨርሲቲው በዘርፉ የሚታዩ ተግዳሮቶችን በምርምር ለመለየት የአምስት ዓመት ሜጋ ፕሮጀክት ጥናት እያካሄደ እንደሚገኝም አስታውሰዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዞኑን እምቅ አቅም በይፋ መጥቀሳቸው፣ ለዘርፉ መነቃቃት ትልቅ አቅም መሆኑን ገልጸው፤ የግንባታ ሥራቸው የተጀመሩ የቱሪዝም መሠረተ ልማቶች ሲሟሉ ዘርፉ የኢኮኖሚው ምሰሶ እንደሚሆን ገልጸዋል። የባሌ ዞን ብዙም ባልተራራቁ አካባቢዎች የተለያዩ ዓይነት ሥነ-ምህዳሮች በቀላሉ የሚታዩበትና ለቱሪስት ተመራጭና ተወዳጅ የሆኑ ቅርሶች መገኛ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የዩኒቨርሲቲው መምህርና ተመራማሪ ሀዲስ ታደለ(ዶ/ር) ናቸው። የለውጡ መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት የእነዚህን መስህቦች ልማት ወደ ተግባር በማስገባት ላይ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም የቱሪስቶችን የቆይታ ጊዜ በማራዘም ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ እንደሚያግዝ ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲ ደረጃም ከዚህ በፊት በዋናነት ከሚታወቁት ዋና ዋና ቅርሶች ባሻገር ከ100 በላይ አዳዲስ ቅርሶች በጥናት መለየታቸውንና የተለዩት ቅርሶችም በሳይንሱ ዓለም እንዲታወቁ ዲጂታል ካርታ የተዘጋጀላቸው መሆኑን አመልክተዋል። በተለይም የዩኒቨርሲቲ ምሁራን እያካሄዱ በሚገኙት ጥናት በባሌ፣ ምሥራቅ ባሌና ምዕራብ አርሲ አካባቢ የሚገኙ የተለያዩ የተፈጥሮ፣ ሰው ሰራሽና ታሪካዊ የመስህብ ስፍራዎች ተለይተው፣ ዶክመንት ተሰንዶላቸው መቀመጣቸውን ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል። በአጠቃላይ፣ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የቱሪዝም ኢኒሼቲቭ ለዘርፉ ትልቅ መነሳሳትን የፈጠረ መሆኑን የጠቆሙት ምሁራኑ፣ የባሌ ዞንን የተፈጥሮና ባህላዊ ሃብቶችን በማዘመንና በምርምር በማገዝ የሀገሪቱን የቱሪዝም ገጽታ ለመቀየር በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የፈረንሳይ ሊዮን የበረራ አገልግሎት አፍሪካን ከዓለም ለማገናኘት በሚደረገው ጉዞ ቁልፍ ምዕራፍ ነው
Jul 1, 2026 1177
‎አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):-‎የኢትዮጵያ አየር መንገድ የፈረንሳይ ሊዮን የበረራ አገልግሎት አፍሪካን ከዓለም ለማገናኘት በሚደረገው ጉዞ በቁልፍ ምዕራፍነት እንደሚወሰድ የአየር መንገድ ግሩፑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን አዲስ የመንገደኞች በረራ አገልግሎትን አስጀምሯል።   የአየር መንገድ ግሩፑ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በዚሁ ወቅት፤ የፈረንሳይ የኢኮኖሚ፣ የባህልና የፈጠራ ብልፅግና ማዕከሏ ሊዮን የሚደረገው በረራ የተደራሽነት አድማስን ያሰፋል ብለዋል። ወደ ሊዮን ከተማ የሚደርገው በረራም የአውሮፓ መዳረሻውን ወደ 23ኛ በማሳደግ የፈረንሳይ ከተሞች ከአፍሪካ ጋር በማገናኘት ስኬታማ ሥራ እየተሰራ መሆኑን እንደሚያሳይ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንድ በፈረንሳይና የአውሮፓ ከተሞች የሚያደርገው የበረራ አገልግሎትም የኢትዮ-አውሮፓን ግንኙነት በማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል።   አየር መንገዱ ለደንበኞቹ በሚያቀርባቸው ጥራትና ብቃት ያላቸው የበረራ አገልግሎቶችም ዓለም አቀፍ የአቭዬሽን ኢንዱስትሪ ስመጥሩነቱን በተግባር እያስመሰከረ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በሚቀጥለው በጀት ዓመትም አምስት አዳዲስ የበረራ አገልግሎትን በማስጀመር ኢትዮጵያና አፍሪካን በዓለም የንግድ፣ ቱሪዝምና ኢንቨስትመንት ዘርፍ የማስተሳሰር ሚናውን እንደሚወጣ አረጋግጠዋል። አየር መንገዱ የበረራ አገልግሎት ጥራትን ለማላቅም ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በላቀ ቴክኖሎጂዎችና በደንበኛ ተኮር አገልግሎት ላይ ሰፊ ኢንቨስትመንት እያደረገ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ወደ ፈረንሳይ ሊዮን ለሚደረገው የበረራ አገልግሎት መሳካት ድጋፍና ትብብር ላደረጉ ባለድርሻ አካላትም ምስጋና አቅርበዋል።   በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ በበኩላቸው፤ አየር መንገዱ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን ያስጀመረው የበረራ አገልግሎት የሀገራቱን ሁለንተናዊ ግንኙነት ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። በተለይም የኢትዮ-ፈረንሳይን ጠንካራ የዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነት በህዝብ ለህዝብ ትስስር፣ በንግድና ኢንቨስትመንት ለማጠናከር እንደሚረዳ አስረድተዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀመረ
Jul 1, 2026 886
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):-‎የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን አዲስ የመንገደኞች በረራ ጀምሯል። ‎በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ‎የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው፣ በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ እንዲሁም የአየር መንገዱ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ታድመዋል። ‎የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በረራው የሀገራቱን ግንኙነት የሚያጎለብት ነው።   በኢትዮጵያና በፈረንሳይ መካከል ያለውን የንግድ፣ ቱሪዝም እና የባህል ልውውጥ የሚያሳድግ መሆኑንም ጠቁመዋል። ‎አየር መንገዱ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን የሚያደርገው በረራ በአውሮፓ 23ኛ መዳረሻው መሆኑን ገልጸዋል።   በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ በበኩላቸው፤ አየር መንገዱ ወደ ፈረንሳይ ሊዮን ያስጀመረው በረራ የሀገራቱን የንግድና ቱሪዝም ግንኙነት በማሳደግ ረገድ ትልቅ ምዕራፍ የሚከፍት መሆኑን ገልጸዋል። ሊዮን የፈረንሳይ ሁለተኛዋ የኢኮኖሚ ማእከል መሆኗን ጠቅሰዋል።
የሀዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማት ከሐይቁ የተፈጥሮ ውበት ጋር ተሰናስሎ በልዩ ዲዛይን በላቀ ጥራት እየተገነባ ነው
Jul 1, 2026 589
‎ሀዋሳ፤ ሰኔ 24/ 2018 (ኢዜአ):-የሀዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማት ከሐይቁ የተፈጥሮ ውበት ጋር ተሰናስሎ በልዩ ዲዛይን በላቀ ጥራት እየተገነባ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለጹ። የከተማዋ ነዋሪዎች በበኩላቸው ለከተማዋ የኮሪደርና የሐይቅ ዳርቻ ልማት ሥራዎች የሚጠበቅባቸውን በመወጣት ታሪካዊ አሻራቸውን እንደሚያሳርፉ ገልጸዋል። ሀገራዊ የኮሪደር ልማት ኢኒሺዬቲቭ መተግበር ከተጀመረ በኋላ ከተሞች ውብ ገፅታና ዘመናዊነትን ከመላበስ ባለፈ ለኑሮና ለንግድ እንቅስቃሴ ምቹ እየሆኑ ይገኛሉ፡፡ በሃዋሳ ከተማ ደግሞ ልማቱ ከተማዋ የቱሪስት መዳረሻነቷ ከፍ እንዲል፣ ለኑሮም ምቹ እንድትሆንና ውበቷም ይበልጥ እንዲጎላ እያደረጋት ነው።   በቅርቡም ከኮሪደር ልማቱ በተጨማሪ የተፈጥሮ ጸጋዎቿ እንዲገለጡ የሚያደርግና ከኮሪደር ጋር የተሰናሰለ የሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት በይፋ ተጀምሯል፡፡ ፕሮጀክቱን በማስመልከት ኢዜአ ያነጋገራቸው የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ አቶ ጥራቱ በየነ እንዳሉት፤ የሀዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማት ከሐይቁ የተፈጥሮ ውበት ጋር ተሰናስሎ በልዩ ዲዛይን በላቀ ጥራት እየተከናወነ ነው። የሐይቅ ዳርቻ ልማቱ የከተማዋን የኮንፈረንስ ማዕከልነት እንዲሁም የጎብኚዎቿን የቆይታ ጊዜ እንደሚያራዝመው አንስተዋል፡፡ ፕሮጀክቱ የማህበረሰቡ አሻራ በጉልህ እንዲያርፍ ታስቦ መጀመሩን የገለጹት ከንቲባው 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በጀት እንደተያዘለትና ህብረተሰቡም በአቅሙ አስተዋጽኦ በማድረግ የድርሻውን እንዲወጣ አመልክተዋል። እንደ ከንቲባ ጥራቱ ገለጻ፤ በከተማዋ በ2ኛ እና በ3ኛ ዙር 8 ነጥብ 9 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የኮሪደር ልማት ሥራ ተከናውኗል። ልማቱም የብስክሌት፣ የሞተር ብስክሌትና የመኪና ማቆሚያዎች፣ የታክሲ መጫኛና ማውረጃ፣ የሕፃናት መጫወቻዎችንና የወጣቶች የስፖርት ማዘውተሪያዎች አካቶ የተከናወነ መሆኑንም አመልክተዋል። በአሁን ወቅት 4 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው አራተኛው ዙር የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ ልማቱም ከሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ጋር መሰናሰሉን አመልክተዋል። የሀዋሳ ከተማ ነዋሪዎች በበኩላቸው፤ በከተማዋ እየተከናወኑ ባሉ የኮሪደርና የሐይቅ ዳርቻ ልማት ሥራዎች የሚጠበቅባቸውን በመወጣት ታሪካዊ አሻራቸውን እንደሚያሳርፉ አረጋግጠዋል።   ከነዋሪዎቹ መካከል ወይዘሮ ያምሮት ኃይሌ የኮሪደር ልማቱ ሀዋሳ ድሮ ከነበራት ውበት በላይ እንዳደመቃትና ተወዳዳሪ እንዳደረጋት ተናግረዋል። በሆቴል ሥራ ዘርፍ የተሰማሩት አቶ ለገሰ ላሚሶ በበኩላቸው፤ በከተማዋ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ሥራ በተለይ የሆቴል ዘርፉ እንዲነቃቃ የጎላ ሚና እንዳለው ተናግረዋል።   ወደ ሀዋሳ የሚመጡ እንግዶችን በላቀ መስተንግዶ ተቀብለው ለማስተናገድ ይበልጥ መነቃቃታቸውን ገልጸው፣ የተጀመረው የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ተጠናቆ ከተማዋ ይበልጥ እንድታድግ የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስታውቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም