ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የመደመር መንግሥት የኢትዮጵያን የቅርስ ሃብቶች በዘላቂነት በመጠበቅና በማልማት ለትውልድ የሚሻገር አስደናቂ ሥራ ሰርቷል
Jul 6, 2026 28
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29/2018(ኢዜአ)፦ የመደመር መንግሥት የኢትዮጵያን የታሪክ፣ የተፈጥሮና ባህላዊ የቅርስ ሃብቶች በዘላቂነት በመጠበቅና በማልማት ለትውልድ የሚሻገር አስደናቂ ሥራ መስራቱን የኢትዮጵያ ቅርስ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር አበባው አያሌው ገለጹ። ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮችና የዓለምአቀፍ ተቋማት መሪዎች ከፍተኛ የዲፕሎማቶች ልዑክ በላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ጉብኝት አድርገዋል።   የዲፕሎማቲክ ልዑካን የላሊበላ ጉብኝት የኢትዮጵያን የቱሪዝም ዕምቅ አቅም ለዓለም ለማስተዋወቅና በቅርስ ጥበቃ የሚደረገውን ዓለምአቀፍ ድጋፍ ለማጠናከር ትልቅ አስተዋጽኦ አለው። የኢትዮጵያ ቅርስ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ረዳት ፕሮፌሰር አበባው አያሌው ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ኢትዮጵያ የአስደናቂ ኃይማኖታዊ፣ ታሪካዊ፣ ተፈጥሯዊና ባህላዊ ቅርሶች ባለቤት ናት። በተባበሩት መንግስታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት(ዩኒስኮ) የተመዘገበው የላሊባላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የኪነ-ሕንፃ የአሰራር ጥበብ ዓለምን ያስደመመ ድንቅ የጥበብ ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። የላሊበላን ቅርስም ለኃይማኖታዊ ሥርዓትና ዓለምአቀፍ ጎብኚዎች ምቹ ለማድረግ ከፈረንሳይ መንግሥት ጋር የዘላቂ ቅርስ ጥበቃ መሠረተ ልማት ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የኪነ-ሕንፃ ጥበብ ከመጠበቅ ባሻገርም የአብያተ ክርስቲያናቱን የካበቱና ውድ የሥነ-ጽሑፍ ሃብቶች ዲጂታላይዝ በማድረግ ለተተኪ ትውልድ ለማስተላለፍ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን ታሪካዊ፣ ተፈጥሯዊ እና ባህላዊ ሃብቶች ለመጠበቅ፣ ለመንከባከብና ለማልማት የሰጡት ትኩረት የቅርስ ጥበቃ ውጤታማነትን አሳድጓል ብለዋል። የጎንደር አፄ ፋሲለደስ አብያተ መንግሥታት፣ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት እና የጅማ አባጅፋር ቤተ-መንግሥት ዕድሳት የመደመር መንግሥት ድንቅ ሥራ አብነቶች መሆናቸውን አስረድተዋል።   የዘላቂ ቅርስ በኢትዮጵያ ፕሮጀክት ኃላፊ ኪዳነማርያም ወልደ ጊዮርጊስ በበኩላቸው፣ በላሊበላ ውቅር አብያተ-ክርስቲያናት ቅርስ ጥበቃ ፕሮጀክት ሥር ሰፋፊ መሠረተ ልማትቶች መካተታቸውን አረጋግጠዋል። የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የቅርስ ጥበቃ ፕሮጀክትም ቅርሱን ጠብቆ ለቀጣዩ ትወልድ ለማሻገር ትልቅ ዕድል መሆኑንና ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል የፈጠረ መሆኑን ገልጸዋል።   የዲፕሎማቲክ ልዑካን ቡድን አባላት የላሊበላ ጉብኝት የኢትዮጵያን የቱሪዝም ዘርፍ ማንሰራራት የሚያረጋግጥ ነው ያሉት ደግሞ የላሊበላ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ መሳይ ወዳጆ ናቸው። የመደመር መንግሥት ለቱሪዝም ዘርፍ የሰጠው ትኩረት የላሊበላን ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ቅርስ በመጠበቅ፣ በማልማትና በመንከባከብ ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ የሚያስችል ዕድል መፍጠሩን ተናግረዋል።
የሀብት ማከፋፈያ ቀመሮች በአግባቡ መተግበራቸውን በቅርበት መከታተል ተችሏል- አቶ ሽመልስ አብዲሳ
Jul 5, 2026 928
አዲስ አበባ፣ሰኔ 28/2018 (ኢዜአ)፦በበጀት ዓመቱ የሀብት ማከፋፈያ ቀመሮች በአግባቡ መተግበራቸውን በቅርበት መከታተል መቻሉን የፌዴሬሽን ምክር ቤት የድጎማ በጀትና የጋራ ገቢዎች ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። አቶ ሽመልስ አብዲሳ እንዳሉት በ2018 በጀት ዓመት በክልሎች መካከል የተመጣጠነ ልማትንና የዜጎችን ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በርካታ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል። የድጎማ በጀትና የጋራ ገቢዎች ክፍፍል ሥርዓት በጥናትና በተደራጀ ዕቅድ እንዲመራ ከማድረግ ባሻገር ወደ ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የሚተላለፉ ሀብቶች ግልጽና ፍትሐዊ በሆነ መንገድ እንዲከፋፈሉ ክትትልና ድጋፍ መደረጉን ተናግረዋል።   በበጀት ዓመቱ የሀብት ማከፋፈያ ቀመሮች በአግባቡ መተግበራቸውን በቅርበት መከታተል መቻሉን ገልጸዋል። ይህም የሚተላለፉ ሀብቶች ላይ ግልጽነትን ለማሳደግና የበይነ መንግሥታት የፊስካል ሽግግር ሥርዓትን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አብራርተዋል። በተጨማሪም የፌዴራል መሠረተ ልማት ስርጭት ፍትሐዊነትን ማስፈን እንዲሁም ልዩ ዓላማ ያላቸው ድጎማዎች በግልጽነትና በተጠያቂነት መርህ ለክልሎች መከፋፈላቸውን ማረጋገጥ የኮሚቴው ዋና ዋና ስትራቴጂካዊ ተግባራት እንደነበሩ አመልክተዋል። የኢኮኖሚና የማሕበራዊ ዕድገትን ማፋጠንና በክልሎች መካከል ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን እውን ማድረግ የረጅም ጊዜ ጥረት እንደሚጠይቅ ገልጸው ማነቆዎችን በመለየትና መረጃዎችን በወቅቱ በማሰባሰብ ዘላቂ መፍትሔዎችን ለማምጣት ይሰራል ማለታቸውን የፌዴሬሽን ምክር ቤት መረጃ ያመለክታል።
በክልሉ የምርት ግብዓት ቁጥጥርን በማጠናከር ምርታማነትን ለማላቅ በተከናወነ ተግባር ውጤት ተገኝቷል
Jul 5, 2026 279
ባህርዳር፤ ሰኔ 28/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የእርሻ ምርት ግብዓት ቁጥጥርን በማጠናከር ምርታማነትን ለማላቅ በተከናወነ ተግባር ውጤት መገኘቱን የክልሉ የግብርና ጥራትና ቁጥጥር ባለሥልጣን አስታወቀ። የክልሉ የግብርና ጥራትና ቁጥጥር ባለሥልጣን የ2018 በጀት ዓመት የዕቅድና አፈፃፀም መድረክን በባህር ዳር ከተማ ዛሬ አካሄዷል። በወቅቱም የአማራ ክልል የግብርና ጥራትና ቁጥጥር ባለሥልጣን ኃላፊ አቶ ፈንታሁን ስጦታው እንደገለጹት፤ ባለሥልጣኑ በዘር፣ በማዳበሪያ፣ በፀረ-አረም ኬሚካል፣ በመጤ አረምና በሌሎች የግብርና ግብዓቶች ላይ የጥራትና ቁጥጥር ሥራ እያከናወነ ይገኛል። በዚህም በክልሉ የእርሻ ምርት ግብዓት ቁጥጥርን በማጠናከር ምርታማነትን ለማላቅ በተከናወነ ተግባር ውጤት ተገኝቷል ብለዋል። ለአብነትም በበጀት ዓመቱ ከ10 ሺህ 800 ሄክታር በላይ በምርጥ ዘር በተሸፈነ መሬት ላይ ቁጥጥር በማድረግ፣ ከ600 ሄክታር በላይ የተዘራው ዘር የጥራት ደረጃውን ባለማሟላቱ ውድቅ መደረጉን አንስተዋል። በተለይም በመሰብሰብ፣ በማከማቸት፣ በማጓጓዝና በማሰራጨት ላይ የሚከሰትን የጥራት መጓደል ለመቀነስ ለባለድርሻ አካላት ሰፊ ግንዛቤ ተፈጥሮ ወደ ሥራ በመገባቱ አበረታች ውጤት መመዝገቡን አስረድተዋል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ግብርና ጥራትና ቁጥጥር ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ ብርሃኔ ገብሬ በበኩላቸው ሥራው በምሥራቅ አማራ በሚገኙ በዋግ ኸምራና በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደሮች፣ በሰሜንና በደቡብ ወሎ ዞኖች ላይ በማተኮር መሠራቱን ገልጸዋል። በነዚህ ዞኖች በዘር ብዜት ላይ የተሰማሩ ስምንት ድርጅቶች ላይ ከማሳ ጀምሮ ተገቢውን የዘር ጥራትና ቁጥጥር በማድረግ፣ ከ20 ሺህ ኩንታል በላይ ጥራቱን የጠበቀ ምርጥ ዘር ማቅረብ መቻሉን ተናግረዋል። በቀጣይም የግብዓት ጥራት፣ ደህንነትና ቁጥጥር ተግባሩን አጠናክሮ ለማስቀጠል ከባለድርሻ አካላት ጋር የተጀመረው ቅንጅታዊ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በውይይቱ ላይ የተገኙት የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ አጀበ ስንሻው በክልሉ ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ለወጪ ንግድና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆን ምርት ለማምረት እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። ጥራቱ የተረጋገጠ ምርጥ ዘር፣ ማዳበሪያና ሌሎች ግብዓቶችን ለአርሶ አደሩና ለባለሀብቱ በወቅቱ ማቅረብ ለግብርናው ዘርፍ ምርታማነት ማደግ መሠረት መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የሚመረተውን ምርጥ ዘር ወደ ውጭ ለመላክና ለማስገባት፣ በሥርዓተ ምግብ በኩልም የሰውን ጤና የማይጎዳ ምርት ኃላፊነት በተሞላበት ሁኔታ ለማቅረብ እንደሚያስችል አስረድተዋል። በዚህም ባለሥልጣኑ የግብርና ግብዓትን ጥራት በማሳ ላይና በላቦራቶሪ በመመርመር እንዲሁም የላቀ ቁጥጥር በማድረግ እያከናወነ ያለው ሥራ የሚበረታታ በመሆኑ ተጠናክሮ እንዲቀጥልም አሳስበዋል። በመድረኩ ላይ የባለሥልጣኑ እና የዞን ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊዎች፣ ከፍተኛ ባለሙያዎች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።  
የሀዋሳ ከተማ የኮሪደርና የሀይቅ ዳርቻ ልማት የጎብኚዎችን የቆይታ ጊዜ እያራዘመ ነው
Jul 5, 2026 294
ሀዋሳ ፤ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ) :- የሀዋሳ ከተማ የኮሪደርና የሀይቅ ዳርቻ ልማት የጎብኚዎችን ቀልብ በመሳብ የቆይታ ጊዜያቸውን እያራዘመው እንደሚገኝ የሲዳማ ክልል ባህል፣ ቱሪዝምና ስፖርት ቢሮ ገለጸ።   በሲዳማ ክልል ታሪካዊና የተፈጥሮና የቱሪስት መስህቦችን በማልማትና በማስተዋወቅ ረገድ በተሰራው ሥራ፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ3 ሚሊዮን 280 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጪ ቱሪስቶች ክልሉን መጎብኘታቸውን ቢሮው ገልጿል።   የቢሮው ምክትል ኃላፊና የቱሪዝም ዘርፍ ኃላፊ አቶ አበበ ማሪሞ ለኢዜአ እንደገለፁት የቱሪስት መስህቦችን በማልማት ኢኮኖሚያዊ ፋይዳቸውን ለማጉላት ሰፊ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ። ለዚህም በአብነትነት የሀዋሳ ፍቅር ሐይቅን፣ የጋራንባ ተራራ ባህላዊ ሎጅን፣ የሲዳማ አፊኒ ሶንጎ ባህላዊ የፍትሕ ሥርዓት ማከናወኛ ስፍራን፣ የተፈጥሮ ፍል ውኃ ስፍራዎችንና ፏፏቴዎችን ጠቅሰዋል።   በተለይም የሀዋሳ ከተማ የኮሪደር ልማትና የሐይቅ ዳርቻ ልማት የጎብኚዎችን የቆይታ ጊዜ በማራዘም ከዘርፉ የሚገኘው ገቢ እንዲጨምር ማድረጉን አቶ አበበ አንስተዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ ክልሉን ከ3 ሚሊዮን 280 ሺህ በላይ የሀገር ውስጥና የውጭ ቱሪስቶች መጎብኘታቸውንና ከዚህም 3 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ገልጸዋል።   ከአዲስ አበባ ሀዋሳን ለመጎብኘት የመጡት አቶ ዘላለም ተስፋዬ በሰጡት አስተያየት፤ የሀዋሳ ከተማ ዕድገት፣ የኮሪደር ልማቱና የሐይቅ ዳርቻ ማሻሻያው የቱሪስቶችን ቀልብ መሳብ የሚችሉና ከተማዋን ተመራጭ መዳረሻ የሚያደርጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። የሀዋሳ ከተማን ለእረፍት ጊዜያቸው ዘወትር እንደሚመርጧት የገለጹት ደግሞ ሰላማዊት እሸቱ ናቸው።   ለዚህም የከተማዋ ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ የቱሪስት መዳረሻዎች፣ እንዲሁም የሐይቅ ዳርቻ ልማቱ ከተማዋን ይበልጥ ሳቢና ማራኪ እንዳደረጋትም አስረድተዋል።
የሕዝብን የልማት ጥያቄዎች በጥናት ላይ ተመስርቶ በፍጥነት ለመመለስ ትኩረት ተሰጥቷል-አብዱ ሁሴን (ዶ/ር)
Jul 5, 2026 623
ደሴ፤ሰኔ 28/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በቀጣዮቹ ዘጠና ቀናት የሕዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በጥናት ላይ ተመስርቶ በፍጥነት ለመመለስ በትኩረት እንደሚሰራ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለጹ። በዘጠና ቀናት ዕቅድና አፈጻጸም ላይ የክልሉ የሥራ ኃላፊዎች በደሴ ከተማ ውይይት እያካሄዱ ነው።   የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ የክልሉን ዕድገትና የሕብረተሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጠናከረ አመራር በመስጠት በትኩረት እየተሠራ ይገኛል። በክልሉ በቀጣዮቹ ዘጠና ቀናት የሕዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በጥናት ላይ ተመስርቶ በፍጥነት ለመመለስ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። በዚህም የክረምት ሥራዎችን ጨምሮ በዋና ዋና የልማት ዘርፎች ላይ በመረባረብ፣ የተጀመረውን ዕድገትና ብልፅግና ዳር ለማድረስ በቁርጠኝነት እንደሚሰራም አክለዋል።   በተለይም በየደረጃው ያለው አመራር የመረጠውን ሕዝብ በላቀ ሁኔታ ለማገልገልና ተጠቃሚ ለማድረግ በቁርጠኝነት መሥራት እንዳለበት አሳስበዋል። ለዚህም የመንግሥትን አፈጻጸም በሁሉም ዘርፍ ማሳደግ፣የኑሮ ውድነቱን ማረጋጋት፣ የዜጎችን ገቢ ማላቅና የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎትን ማስፋፋት ላይ በማተኮር ችግሮችን የመፍታት አቅጣጫ መከተል እንደሚያስፈልግም አብራርተዋል። የክልሉን ሰላም ለማጽናት በተደረገው ጥረት ውጤታማ ተግባር መከናወኑን የጠቆሙት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ፥ በቀጣይም ሰላሙን በዘላቂነት በመጠበቅ ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ የማድረግ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በመድረኩም ላይ የክልል፣የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራሮች እንዲሁም ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ ነው።
ሀዋሳ ከተማን የኢንዱስትሪና የአገልግሎት ማዕከል ለማድረግ እየተሰራ ነው 
Jul 4, 2026 1204
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦የሀዋሳ ከተማን የኢንዱስትሪና የአገልግሎት ማዕከል ለማድረግ እየተሰራ ነው ሲሉ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ ገለፁ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት፣ የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት የሀብት ማሰባሰቢያ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በዚህ ወቅት፤ የሲዳማ ክልል የሀዋሳ ከተማን የኢንዱስትሪና የአገልግሎት ማዕከል ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ባለሀብቶች ወደ ሀዋሳ በመምጣት እውቀትና ሀብታቸውን ተጠቅመው በኢንቨስትመንት እንዲሰማሩ ርዕሰ መስተዳድሩ ጥሪ አቅርበዋል። ሀዋሳ መተላለፊያና ማረፊያ ከተማ በመሆኗ ባለሃብቶች በአካባቢው ያለውን ዕድል እንዲጠቀሙ ጠይቀዋል። ሀዋሳን በጋራ ለመገንባት የቀረበውን ጥሪ ተቀብለው በቁርጠኝነት ለሰሩና የበኩላቸውን ሚና ለተወጡም ምስጋና አቅርበዋል። ሀዋሳ የደቡብ ፈርጥ፣ የሰላም ደሴት፣ ባላት ውብ ተፈጥሮ ምድረ ገነት የተባለች፣ እንዲሁም የህዝቡ እንግዳ ተቀባይነት የፍቅር ቤት ያስባላት ከተማ መሆኗን አንስተዋል። ሀዋሳን ለኑሮ፣ ለመዝናኛ፣ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት የተመቸች ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። የሀዋሳ ከተማ ከንቲባ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው፣ የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት የሀብት ማሰባሰቢያ መድረክ የፕሮጀክት መገንቢያ ብቻ ሳይሆን፣ የነገንና አዲሱን ምዕራፍ በጋራ ለመገንባት መሆኑን ገልጸዋል።   ሀዋሳ በተፈጥሮ የታደለች ናት ያሉት ከንቲባው፤ ከተማዋን አልምቶ ለትውልድ ማስተላለፍ እንደሚገባ ተናግረዋል። የሀዋሳ ሐይቅ የቱሪዝም ምንጭና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያለው መሆኑን አንስተው፤ የሐይቁን ዳርቻ ማልማት የከተማዋን ገጽታና ተስፋ የሚቀይር ታሪካዊ ስራ መሆኑንም ገልጸዋል። ሀዋሳን ለኑሮ፣ ለኢንቨስትመንት፣ ለቱሪዝም ምቹ እንዲሁም ከተማዋን የአፍሪካ የቱሪዝምና የኮንፍረንስ ማዕከል ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት የፍቅር ሐይቅ፣ አሞራ ገደልና ዓሳ ገበያን ለነዋሪዎቿና ለቱሪስቶች ምቹ ለማድረግ መታቀዱንም ተናግረዋል። ከተማዋን በዘመናዊ መንገድ ለመገንባት ለተወጠነው ፕሮጀክት ከሦስት ነጥብ አምስት ቢሊዮን ብር በላይ በጀት እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው፤ ከዚህ መካከል ሁለት ቢሊዮን ብር ከከተማ አስተዳደሩ፣ አንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን ብሩን በገቢ ማሰባሰቢያ ለማግኘት መታቀዱን አስረድተዋል። ባለፉት ሁለት ወራት በቀረበው ጥሪ መሰረት በመጀመሪያው ዙር የሀብት ማሰባሰቢያ ድጋፍ ሲደረግ መቆየቱን ጠቅሰው፤ የዛሬው መድረክም የመጀመሪያ ዙር የሀብት ማሰባሰቢያ ማጠናቀቂያ መሆኑን ተናግረዋል። የሀዋሳ ሐይቅን ለማልማት የከተማዋ ነዋሪዎች፣ ባለሃብቶችና ባለድርሻ አካላት ድጋፍ ማድረጋቸውንም ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ የድህነትና ኋላቀርነት ታሪክን በሚሰብር የመነሳትና የብልፅግና የእጥፋት ዘመን ላይ ናት 
Jul 4, 2026 977
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የድህነትና ኋላቀርነት ታሪክን በሚሰብር የመነሳትና የብልፅግና የእጥፋት ዘመን ላይ ናት ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለፁ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት የሀዋሳ ሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት የሀብት ማሰባሰቢያ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ ሀገራት ከችግርና ጉስቁልና የሚሻገሩበት የእጥፋት ጊዜ አለ። ኢትዮጵያ ያለችበት ዘመን የእጥፋት፣ ብልፅግናና የመነሳት ዘመን መሆኑንም ተናግረዋል። በአዲስ አበባ በመንግስት መሪነት፣ በግል ባለሀብቱ ተሳትፎና ትብብር የተለያዩ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። የሀዋሳ የልማት ፕሮጀክት ትልቅ በጀት የሚጠይቅ፤ ሲጠናቀቅም ለነገ ተጠቃሚነት ማረጋገጫ መሆኑንም ጠቁመዋል።   በሁሉም አካባቢዎች የተጀመሩ የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል። አንድነታችንን እንደጋሻና ጦር በመጠቀም ኢትዮጵያን ከድህነትና ኋላቀርነት የምናላቅቅበትና በጋራ የምናለማበት መጪው ጊዜ ብሩህ ነው ብለዋል። መድረኩ ብልፅግና ፓርቲ የህዝብ ይሁንታ አግኝቶ በተመረጠበትና ለመንግስት ምስረታ እየተዘጋጀ ባለበት ወቅት መዘጋጀቱ ልዩ ትርጉም የሚሰጠው ነው ብለዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በመኸር እርሻ ከ485 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም ይለማል
Jul 4, 2026 867
ደብረ ማርቆስ ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ጎጃም ዞን በመጭው የመኸር ምርት ዘመን ከ485 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም እርሻ እንደሚለማ የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ እንቢአለ አለኽኝ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ በመኸር እርሻ ለማልማት ከታቀደው ከ669 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ውስጥ ከ485 ሺህ ሄክታር የሚሆነው በኩታ ገጠም እንደሚለማ ነው የተናገሩት። በመኸር እርሻ የምርት ማሳደጊያ ግብአት ፣ ቴክኖሎጂና አዳዲስ አሰራሮችን በተሻለ መንገድ ተግባራዊ በማድረግ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ርብርብ እየተደረገ ነው። በዚህም አርሶ አደሩ ከራሱ አልፎ ለገበያ የሚያቀርበው ትርፍ ምርት ለማምረት እንደሚችልም ነው የተናገሩት።   ከ100 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የስንዴ፣ ጤፍ ፣ ማሽላ ፣ የቢራ ገብስ ፣ በቆሎና ቦለቄ ሰብሎችን በኩታ ገጠም ለማልማት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። እስካሁን በተደረገው ጥረትም ክረምቱ ቀድሞ በገባባቸው አካባቢዎች ከ90 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን ተናግረዋል። በኩታ ገጠም ልማቱ ከ20 በላይ ትራክተሮች በእርሻ ስራው ላይ መሰማራታቸውን ጠቁመው ይሕም የአርሶ አደሩን ጊዜ፣ ገንዘብና ጉልበት በመቆጠብ በሌሎች የልማት ስራዎች እንዲሰማራ የሚያደርግ ነው ብለዋል። እስካሁን በኩታ ገጠም በዘር ለተሸፈነው መሬትም ከ250 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ጥቅም ላይ የዋለ ሲሆን ይህም ምርታማነትን በማሳደግ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት የሚያግዝ መሆኑን አስገንዝበዋል። በዞኑ የደብረኤሊያስ ወረዳ የገነቴ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አየነው በቀለ እንደገለጹት፤አንድ ሄክታር መሬታቸውን በኩታ ገጠም በማልማት በቆሎ መዝራታቸውን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመትም በኩታ ገጠም ካለሙት ስንዴና በቆሎ ያገኙትን ተጨማሪ ምርት ለገበያ በማቅረብ የኢኮኖሚ አቅማቸውን ማሳደጋቸውን አስረድተዋል። የደጀን ወረዳ የኩራር ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ያደለው በዛ በበኩላቸው፤ ባለፈው የምርት ዘመን ግማሽ ሄክታር መሬታቸውን በኩታ ገጠም ማሽላ በመዝራት ተጨማሪ የአራት ኩንታል ምርት እንዳገኙ ነው የሚገልጹት። በዘንድሮ ዓመትም ተጠቃሚነታቸውን ለማስፋት በአካባቢው ካሉ አርሶ አደሮች ጋር በጋራ በመሆን በኩታ ገጠም ማሽላን መዝራታቸውን አብራርተዋል። የኩታ ገጠም አሰራር ዘርንና ግብአት አጠቃቀምን በተመሳሳይ ጊዜ ከማካሄድ ባሻገር የሚዛመት የሰብል በሽታን፣ አረምንና ተባይን በጋራ ለመከላከል የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። በዞኑ በመኸር ምርት በአጠቃላይ ከሚለማው ከ669 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ከ26 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት መታቀዱንም ነው ያመለከቱት።
በክልሉ  ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ 
Jul 4, 2026 237
ቦንጋ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የመሬት አያያዝና አጠቃቀምን በማሻሻል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡ በቢሮው የተፈጥሮ ሀብት ልማትና መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ዘርፍ የአየር ንብረት አፈፃፀም የመሬት አያያዝ ፕሮግራም (CALM) የመጀመሪያ ምዕራፍ መዝጊያ መርሃ ግብር አካሂዷል።   የክልሉ የግብርና ቢሮ ኃላፊ አማካሪና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዮሐንስ መላኩ፣ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም ያሉ የውሃ፣ መሬትና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብቶችን መንከባከብ ማልማትና በተገቢዉ ጥቅም ለይ ማዋል ወሳኝ በመሆኑ የተለያዩ ፕሮጀክቶች ተቀርፀው በመተግበር ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከነዚህ ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ በሆነው (CALM) በክልሉ በ40 ወረዳዎች በውሃና መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ላይ በሰራው ስራ ምርት የማይሰጡ አሲዳማ መሬቶች እንዲያገግሙና ምርታማ እንዲሆኑ ትልቅ ሚና መጫወቱን ገልፀዋል። በተጨማሪም በፕሮግራሙ እገዛ አርሶ አደሩ መሬቱን አስይዞ የብድርና ሌሎች አገልግሎቶችን እንዲያገኝ የ2ኛ ዙር መሬት ልኬት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ነው የገለጹት፡፡ ክልሉ የበርካታ የተፈጥሮ ሀብቶች መገኛ በመሆኑ ይህን ሀብት በመንከባከብና ዘላቂነቱን ለማረጋገጥ የሁሉም ባለድርሻ አካላት ርብርብ ያስፈልጋል ብለዋል። በፕሮግራሙ በ199 ተፋሰሶች ከ112 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት ማልማት 53 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ማድረግ እንደተቻለ የገለጹት ደግሞ የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ውብሸት ዘነበ ናቸው ።   እንደ ክልል የመሬት ልኬት ከተካሄደባቸዉ 380 ሺህ ይዞታዎች ውስጥ 200 ሺህ ያህሉ በዚህ ፕሮግራም የተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በቢሮው የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ተረፈ ማሞ በበኩላቸዉ፣ በክልሉ ባለፉት ዓመታት በ40 ወረዳዎች በሁለት መቶ ተፋሰሶች ላይ ማህበራትን በማደራጀት ሲሰራ ቆይቷል ነው ያሉት።   በዚህም አርሶ አደሩ የተለያዩ ፍራፍሬዎችንና የውጭ ምንዛሬ የሚያስገኙ ሰብሎችን በማምረት ተጠቃሚ በመሆን ላይ እንደሚገኝ ነው የገለጹት። በመጀመሪያዉ ምዕራፍ ለተፋሰሱ አርሶ አደሮች ለኑሮ ማሻሻያና ለተለያዩ መሰረተ ልማት ግንባታዎች ከ247 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉን ተናግረዋል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ፕሮጀክቶች አገልግሎት መስጠት ጀመሩ
Jul 4, 2026 129
ነቀምቴ ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ወለጋ ዞን የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቅተዋል። በዞኑ ጂማ አርጆ ወረዳ ከ749 ሚሊዮን ብር በላይ የወጣባቸው የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት በዛሬው እለት ተመርቀዋል። በምረቃው ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል ውሃ እና ኢነርጂ ቢሮ አማካሪ ቡዛዮ ደገፉ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት የሆኑት እነዚህ ፕሮጀክቶች የህብረተሰቡን የረጅም ጊዜ ጥያቄ የሚመልሱ ናቸው። ፕሮጀክቶቹ በተለይም የአገልግሎት አሰጣጡን የሚያቀላጥፉ እና የሚያዘምኑ ከመሆናቸው ባለፈ የተጀመረውን የብልጽግና ጉዞ ለማሳካት ትልቅ አስተዋጽኦ አላቸው ብለዋል። የምስራቅ ወለጋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ደሱ ለሚ በበኩላቸው፣ በዞኑ የህዝቡን የመልካም አስተዳደር፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎች መመለስ የሚያስችሉ የልማት ስራዎች በስፋት እየተተገበሩ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በዞኑ የህዝቡን መሰረታዊ ጥያቄዎች የሚመልሱ ከ400 በላይ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ስራዎች ተጠናቀው በሁለት ዙር እየተመረቁ ይገኛሉ ብለዋል። በጅማ አርጆ ግንባታው ተጠናቆ የተመረቀው የንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት አንዱ መሆኑን ጠቅሰው የማህበረሰቡን የረጅም ጊዜ ችግር በዘላቂነት የሚፈታ መሆኑን ገልጸዋል። የጂማ አርጆ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ጥላሁን ተሰማ እንደገለጹት፤ በወረዳው ብቻ 21 የሚደርሱ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች በ749 ሚሊዮን ብር ግንባታቸው ተጠናቆ ለምርቃት በቅተዋል። የህዝቡን ፍላጎት ለማሟላት የተደረገው የቅርብ ክትትል ፕሮጀክቶቹ በፍጥነት እንዲጠናቀቁ ከማድረጉም በላይ፣ የነዋሪዎችን የዕለት ተዕለት ኑሮ እያቃለለ መሆኑን ጠቁመዋል። የአካባቢው ነዋሪዎችም በተከናወኑት የመሰረተ ልማት ስራዎች ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል።
በሸገር ከተማ የኢንቨስትመንት መስፋፋት የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የኢኮኖሚ ዕድገትን እያፋጠነ ነው
Jul 4, 2026 128
ሸገር ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦በሸገር ከተማ የኢንቨስትመንት መስፋፋት ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የከተማዋን የኢኮኖሚ ዕድገት እያፋጠነው መሆኑን የከተማው አስተዳደር አስታወቀ። አስተዳደሩ ይህንን የገለጸው ባለሀብቶችና ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈው 2ኛው ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ኤክስፖ ፎረም በተካሄደበት ወቅት ነው።   የሸገር ከተማ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) በፎረሙ ላይ እንደተናገሩት፤ በዘርፉ የሚሰጡ የኢንቨስትመንት አገልግሎቶችና የአቀባበል ሥርዓቶችን ለማሻሻል ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ለውጥ ማምጣት ተችሏል። ባለፉት ዓመታት ኢንቨስትመንትን ለማስፋፋት ምቹና ሳቢ ሁኔታዎችን በማመቻቸት የተሻለ ውጤት እየተገኘ መምጣቱንም ገልጸዋል። የኢንቨስትመንት መስፋፋት የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ የኢኮኖሚ ዕድገትን እያፋጠነ መሆኑን ጠቅሰው፣ ከተማዋን የኢንቨስትመንት ማዕከል ለማድረግ የተጀመረው የተቀናጀ አሠራር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የፎረሙ ዋና ዓላማ የኢንቨስትመንትን ውጤታማነት ማሳደግ መሆኑን የጠቀሱት ከንቲባው፤ በመንግሥትም ሆነ በባለሀብቶች በኩል የሚታዩ ጉድለቶችን በውይይት ለይቶ መፍትሔ ማስቀመጥ መቻሉን አስረድተዋል። የሸገር ከተማ የኢንቨስትመንት ጽ/ቤት ኃላፊ ኃይለሚካኤል ዓለሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ከተማዋ የኢንቨስትመንት ማዕከል እንድትሆን የሚያስችሏት በርካታ ምቹ ዕድሎች እንዳሏት ገልጸዋል።   ለአብነትም የከተማዋን የመሬት አስተዳደር በቴክኖሎጂ በማገዝ አሠራሩን ምቹና ቀልጣፋ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህም መሠረት ባለፉት ሦስት ዓመታት 3 ሺህ 869 ብቻ የነበረው የኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ቁጥር፣ በአሁኑ ወቅት በተከናወኑ አበረታች ሥራዎች ወደ 5 ሺህ 200 ማደጉን ኃላፊው ተናግረዋል። ይህም ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ ለከተማዋ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። በፎረሙ ላይ የተሳተፉትና በጨርቃጨርቅ ዘርፍ የተሰማሩት ባለሀብት አቶ ፍቃዱ ጉተማ እንደተናገሩት፤ መድረኩ መዘጋጀቱ ሥራቸውን ለማሳደግ ትልቅ እገዛ ይኖረዋል። በአሁኑ ወቅት በመንግሥት የተፈጠረው ምቹ የሥራ ሁኔታ አበረታች በመሆኑ፣ ሠርቶ ለመለወጥ ከፍተኛ መነቃቃት እንደፈጠረላቸው ገልጸዋል። በፒፒሲ ፕላስቲክ ምርት ዘርፍ የተሰማሩት ወይዘሮ መጽሄት ከተማ በበኩላቸው፤ መንግሥት በፈጠረላቸው ምቹ ሁኔታ ወደ ሥራ በመግባታቸው ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቁመዋል። በዚህም ከራሳቸው ባለፈ ለሌሎች ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውንና በከተማዋ ዕድገት ውስጥም የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የቅርስ ጥበቃና መስህብ መዳረሻ ልማት እመርታ የኢኮኖሚ አቅምን የሚያጎለብት ነው
Jul 4, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የቅርስ ጥበቃና መስህብ መዳረሻ ልማት እመርታ የኢኮኖሚ አቅምን የሚያጎለብት መሆኑን በኢትዮጵያ የፖርቹጋል፣ ካናዳና ሕንድ አምባሳደሮች ገለጹ። በአዲስ አበባ ተቀማጭነታቸውን ያደረጉ የሀገራት አምባሳደሮችና የዓለም አቀፍ ተቋማት የዲፕሎማቲክ ልዑካን ቡድን አባላት የዓለም ቅርስ የሆነው የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ጎብኝተዋል።   በጉብኝቱም ላይ 40 አምባሳደሮች እና ከ10 በላይ የዓለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮች በላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትና የባህል ማዕከል ጉብኝት አድርገዋል። በኢትዮጵያ የፖርቹጋል አምባሳደር ሉዊስ ፔሬስትሬሎ ዶ ናሲሜንቶ በጉብኝቱ ወቅት፤ የቱሪዝም ዘርፍ የኢኮኖሚ አቅምን ለመገንባት የቅርስ ጥበቃ ሥራ ወሳኝ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያም የቱሪዝም ኢኮኖሚ ዕድገትን ለማሳደግ የምታከናውነው የቅርስ ጥበቃና የአዳዲስ መዳረሻ ልማት የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያና ፖርቹጋል መካከል ዘመናት ያስቆጠረውን የዲፕሎማሲ ወዳጅነት ወደላቀ ምዕራፍ ለማሳደግም ቱሪዝምን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች በትብብር እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የካናዳ አምባሳደር ኒኮላስ ሲማርድ በበኩላቸው፤ ላሊበላ ድንቅ የኪነ-ሕንፃ የጥበብ ውጤት መሆኑን በመጀመሪያ ጉብኝታቸው እንደተመለከቱ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ታሪካዊ፣ ባህላዊና ኃይማኖታዊ ቅርሶችም ለቱሪስቶች መንፈስን የሚያድሱና ድንቅ ውበትን የተላበሱ የዓለም ሃብቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። ላሊበላ ድንቅ የጥበብ ውጤት ነው ያሉት አምባሳደሩ፤ ሥፍራውም የመንፈስ ሰላምና እርጋታን የሚቸር ድንቅ መንፈሳዊ ሥፍራ መሆኑን አንስተዋል። በኢትዮጵያ የሕንድ አምባሳደር አምባሳደር አኒል ኩማር ራይ፤ በኢትዮጵያና ሕንድ መካከል ያለው የረጅም ጊዜ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ወዳጅነት በተለያዩ መስኮች ዕድገት እያስመዘገበ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያና ሕንድ ታሪካዊ ወዳጅነትም በጥንታዊ ቅርሶችና ማራኪ የቱሪስት መስህብ መዳረሻ ስፍራዎች እንደሚያመሳስላቸው ገልጸዋል። በጉብኝታቸውም ላሊበላ በዓለም ላይ ድንቅና ታሪካዊ ኪነ-ሕንፃ ጥበቦች መካከል ግንባር ቀደም የሆነ የጥንታዊ ስልጣኔ ትሩፋት መሆኑን ተናግረዋል። የዲፕሎማቲክ ልዑካኑ ጉብኝትም የኢትዮጵያን ድንቅ ቅርሶችን ለዓለም ለማስተዋወቅ ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው አስረድተዋል።  
የቱሪዝም ዘርፉን እድገት ለማጎልበት የተቋማትን ቅንጅታዊ አሠራር ማጠናከር ወሳኝ ነው
Jul 4, 2026 142
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦የቱሪዝም ዘርፉን እድገት ለማጎልበት ወሳኝ የሆነውን የተቋማትን ቅንጅታዊ አሰራር የማጠናከር ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ የፌደራል ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ ከደባርቅ ዩኒቨርሲቲና ከሰመራ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር "በዳሎል-ራስ ዳሽን ኮሪደር የማይበገር ቱሪዝም መገንባት” በሚል መሪ ሀሳብ የቱሪዝም ዕድሎችን በጥናት ለመለየትና ጠንካራ የቱሪዝም ሥርዓት ለመዘርጋት የሚያስችሉ ስትራቴጂካዊ ግብዓቶች ላይ ያተኮረ ዓውደ ጥናት አካሂዷል።   የፌዴራል ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ይታሰብ ስዩም እንደገለጹት፤ የቱሪዝም ዘርፉን ለማሳደግ በርካታ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። ለዘርፉ የላቀ ውጤታማነት የተቋማትና የባለድርሻ አካላት ቅንጅትና ትብብር አስፈላጊ ነው ብለዋል። ይህም የሀብት ብክነትን በመቀነስ፣ የእውቀትና ቴክኖሎጂ ሽግግርን በማሳደግ የማህበረሰቡን እንዲሁም የሀገሪቱን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንደሚያስችል ነው የገለጹት። የደባርቅ እና ሰመራ ዩኒቨርሲቲዎች ከትኩረት መስካቸው መካከል አንዱ የቱሪዝም ዘርፍ በመሆኑ በጋራ በመስራት የምርምር፣ የጥናትና የእውቀት ሽግግር ስራዎችን ማጠናከር እንዲሁም ሀብትን በብቃት መጠቀምን ያለመ ኢኒሼቲቭ መጀመሩን ገልጸዋል። በኢኒሼቲቩም በዓለም ከባህር ጠለል በታች ዝቅተኛውና ሞቃታማውን ዳሎል እንዲሁም ረጅሙንና በቅዝቃዜው የሚታወቀውን የራስ ዳሽን ኮሪደርን እንደ አዲስ የቱሪዝም ብራንድ ለማስተዋወቅ እንደሚሰራ ተናግረዋል። አካባቢዎቹ የእምቅ ተፈጥሯዊና ባህላዊ ሀብቶች መገኛ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። የማህበረሰቡን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ባረጋገጠ መልኩ በአካባቢው ያሉ የቱሪዝም ቁልፍ ተግዳሮቶችን የመለየትና በጥናትና ምርምር የመፍታት ስራዎች ይከናወናሉ ብለዋል።   የሰመራ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት መሀመድ ኡስማን ( ዶ/ር)፤ የቱሪዝም ዘርፉ የሀገሪቱ ኢኮኖሚ የዕድገት ሞተር በመሆኑ ለውጤታማነቱ ሚናችንን እንወጣለን ብለዋል። ቱሪዝምን የሚደግፉ የጥናትና ምርምር፣ የስልጠናና የቴክኖሎጂ ሽግግር ሥራዎችን በማጎልበት የሀገርን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እንደሚሠሩም ተናግረዋል።   የደባርቅ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አስማማው ዘገየ (ዶ/ር)፤ የራስ ዳሽንና የዳሎልን አካባቢ እምቅ የተፈጥሮ ሀብቶችን በጥናትና ምርምር የመጠበቅና የመንከባከብ እንዲሁም በቴክኖሎጂ የመደገፍ ሥራዎች እንደሚከናወኑ ገልጸዋል። የአካባቢውን ሕዝብ ለዓመታት የዘለቁ ማህበራዊ ትስስሮችን እንዲሁም የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያሳድጉ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አንስተዋል።
ላሊበላ የኢትዮጵያንና የአፍሪካን ታላቅነት የሚያሳይ አስደናቂ ህያው ቅርስ ነው - የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች
Jul 4, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ ላሊበላ የኢትዮጵያንና የአፍሪካን ታላቅነት የሚያሳይ የሰው ልጅ አስደናቂና ሕያው የሥራ ውጤት የሆነ ቅርስ መሆኑን ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የሀገራት አምባሳደሮች እና የዓለም አቀፍ ተቋማት የዲፕሎማቲክ ልዑካን ቡድን አባላት ገለጹ። ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የሀገራት አምባሳደሮች እና የዓለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮች የዓለም ቅርስ የሆነውን የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት እና የባህል ማዕከልን ጎብኝተዋል። በዚህ የጉብኝት መርሃ ግብር ላይ 40 አምባሳደሮች እና ከ10 በላይ የሚሆኑ የዓለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮች ተሳትፈዋል። የሀገራት አምባሳደሮች እና የዓለም አቀፍ ተቋማት የዲፕሎማቲክ ልዑካን ቡድን አባላት ለኢዜአ እንደገለጹት የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን በመጎብኘታቸው ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸዋል። በጉብኝቱ ላይ የታደሙት የሜክሲኮ አምባሳደር አሌሃንድሮ ኤስቲቪል በበኩላቸው፣ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን የኪነ-ህንጻ ጥበብ አድንቀዋል። ከመሬት ከአንድ ዓለት ተፈልፍሎ የተሠራና ወደ ሰማይ የሚናገር የአስደናቂ የጥበብ ሚስጥር መገለጫ ነው ብለዋል። እያንዳንዱ ማዕዘን፣ መስኮትና በር ከአንድ ነጠላ ድንጋይ የተቀረጸ በመሆኑ ለዓለም የሚታይ ታላቅ የአንድነት ምልክት መሆኑንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ታላቅ ሀገር መሆኗን፥ እንደ ላሊበላ ያሉ ከምናብ በላይ የሆኑ አስደናቂ የጥበብ፣ የታሪክና የባህል ቅርስ ባለቤት መሆኗን ተመልክተናል ነው ያሉት። በጉብኝቱ ላይ የተሳተፉት የሮማኒያ አምባሳደር ዩሊያና ግሊጋ እንደገለጹት፤ የቅርስ ጥበቃ ስራ ታሪክን ጠብቆ ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ነው። አምባሳደሯ አክለውም የአሁኑን እና የወደፊቱን ጊዜ ለመገንባት ያለፈውን ታሪክ ማወቅ ያስፈልጋል ብለዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ቅርሶችን ለመጠገን እና ለመንከባከብ እያደረገ ያለውን ጥረት በማድነቅ፥ ይህን ዓይነቱን ለትውልድ የሚሻገር ሥራ ሁሉም አጠናክሮ ሊያስቀጥለው ይገባል ነው ያሉት። በአፍሪካ ህብረት የኩባ አምባሳደር ሉካስ ዶሚንጎ በበኩላቸው ላሊበላ የአፍሪካን ታላቅነት በግልጽ የሚያሳይ ህያው ቅርስ መሆኑን ጠቁመዋል። አፍሪካ ለዓለም ሕዝብ ልታሳውቀው የሚገባ ባህል እና ወግ ያላት መሆኑን ያነሱት አምባሳደሩ፣ አህጉሪቱን ሁልጊዜ ከችግር ጋር ብቻ አያይዞ የመግለጽ ሁኔታ መታረም እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል። አፍሪካ በባህልና በወግ እጅግ ባለጸጋ መሆኗን ጠቅሰው፥ ይህንን እውነታ ለማስተዋወቅ ኢትዮጵያ የጀመረችው የቅርስ ጥበቃና የማስተዋወቅ ሥራ በአርዓያነት የሚወሰድ ነው ብለዋል።    
የሀረሪ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት የ2019 በጀት አመት ረቂቅ በጀት ከ12 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በላይ እንዲሆን ወሰነ
Jul 4, 2026 201
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27 /2018 (ኢዜአ)፦ የሀረሪ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት (ካቢኔ) የ2019 ዓ.ም የክልሉ መንግሥት ረቂቅ በጀት ከ12 ቢሊዮን 8 ሚሊዮን ብር በላይ እንዲሆን ውሳኔ አስተላልፏል። ካቢኔው በክልሉ ገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ቢሮ የቀረበለትን የ2019 የበጀት አመት ረቂቅ በጀት ላይ በጥልቀት በመወያየትና ግብዓት በማከል ለክልሉ ምክር ቤት መርቷል። በዚህም መሰረት በክልል ደረጃ ከተያዘው በጀት 60 በመቶ ለካፒታል በጀት የተመደበ ሲሆን 38 በመቶው ደግሞ ለመደበኛ በጀት የሚውል ነው። የበጀቱ ምንጭም በዋናነት በክልሉ ከተለያዩ ገቢዎች የሚሰበሰብ ገቢ እንዲሁም ከፌዴራል መንግሥት በፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀመር ለክልሎች የሚሰጥ ድጎማና ከሌሎች ምንጮች ታሳቢ መደረጉ ተገልጿል። በጀቱ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀርም የ33 በመቶ ብልጫ አለው። የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ እንዳሉት፤ በ2018 የበጀት አመት ተጀምረው ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶች እንዲጠናቀቁና ወደ ሥራ እንዲገቡ የማድረግ ስራ ትኩረት ይሰጣል። በተለይም በገጠርና በከተማ የሕዝብን የመሰረተ ልማት ጥያቄ ሊመልሱ በሚችሉ ተግባራት ላይ ልዩ ትኩረት እንደተሰጠው ገልጸዋል። ለገጠር እና ለከተማ ኮሪደር ልማት፣ ለንፁህ መጠጥ ውሃ፣ ለትምህርትና ጤና ትኩረት ተሰጥቶ ይሰራል ብለዋል። በጀቱ ቁጠባን መሰረት በማድረግ በተለይም የህዝቡን ህይወት በሚያሻሽሉና መሰረታዊ ጥያቄ በሚመልሱ መልኩ ጥቅም ላይ እንዲውል ለማስቻል አስፈላጊውን ክትትልና ቁጥጥር ይደረጋል ነው ያሉት። በድህነት ቅነሳ ዘርፎች ላይ ርብርብ እንደሚደረግም አመላክተዋል። በወረዳ ደረጃ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ስራ ለማስጀመር ልዩ ትኩረት እንደሚሰጥ ያመላከቱት ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህም ለህብረተሰቡ ፈጣን፣ ፍትሃዊና ጥራት ያለው አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላል ብለዋል። በክልሉ ገቢን አሟጦ ከመሰብሰብ አንፃር በትኩረት መንቀሳቀስ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው ለዚህም የክልሉ ኢኮኖሚ በሚያመነጨው ልክ በታቀደው ልክ መሰብሰብ እንደሚገባ ተናግረዋል። ምክር ቤቱም በቀረበው የ2019 ረቂቅ በጀት አዋጅ ላይ ከተወያየ በኋላ ግብአቶችን በማከል ነው ወደ ክልሉ ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል።
በዞኑ ከ20 ሺህ ለሚበልጡ ወጣቶች የስራ ዕድል ተፈጥሯል 
Jul 4, 2026 216
ሚዛን አማን፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በቤንች ሸኮ ዞን በበጀት ዓመቱ ከ20 ሺህ ለሚበልጡ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን የዞኑ ሥራና ክህሎት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ኮጁ በዳካች ለኢዜአ እንዳሉት፤ የአካባቢውን ጸጋ መሠረት በማድረግ የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንዲቻል የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው። በዚህም በ2018 በጀት ዓመት ከ20 ሺህ የሚበልጡ ወጣቶችን የስራ እድል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ነው የተናገሩት። የስራ እድል የተፈጠረላቸው ዜጎች በግብርና ፣ በማኑፋክቸሪንግ እና አገልግሎት ዘርፍ እንዲሰማሩ በማድረግ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ማረጋገጥ መቻሉን ገልጸዋል።   የወጣቶች የስራ ዕድል ፈጠራን ለማጠናከርም የመስሪያና መሸጫ ቦታ፣ የመነሻ ብድር ፣ የገበያ ትስስር ፣ የህይወት ክህሎት ስልጠናን ጨምሮ በተቀናጀ መልኩ የተከናወኑት የክትትልና ድጋፍ ስራዎች ውጤት አስገኝተዋል ብለዋል። በበጀት ዓመቱ ወደስራ ለገቡ ወጣቶች ከ163 ሚሊዮን ብር በላይ ብድር መሰራጨቱንም ነው የጠቀሱት። የአካባቢውን ጸጋ በማልማት ወደ ሀብት ቀይሮ መጠቀም እንዲቻል በግብርና ላይ ትኩረት መደረጉን ጠቅሰው፤ ወጣቶቹ በተለይ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ላይ በስፋት መሰማራታቸው ስኬት እንዲመዘገብ አድርጓል ብለዋል። ከሥራ ዕድል ተጠቃሚዎች መካከል በሚዛን አማን ከተማ የ"ዕድገት ዶሮ እርባታ" ማኅበር ሰብሳቢ ወጣት ገበየሁ ሽፈራው ከተማ አስተዳደሩ ባመቻቸላቸው የመስሪያ ቦታ በመጠቀም 1 ሺህ የሥጋና የእንቁላል ዶሮዎችን እያረቡ መሆኑን ተናግሯል።   በተሰማሩበት መስክ ተጠቃሚ ከመሆን ባለፈ የዘርፉን ገበያ ለማረጋጋት እየተቻለ መሆኑን ነው ያስታወቀው። በቀጣይም ስራውን በማስፋት የበግና የወተት ላሞች እርባታ ላይ ለመሰማራት ማቀዳቸውን ነው ያመለከተው። የ"ዕድገት ለሰላም" ማኅበር ሰብሳቢ ሚሚ በላቸው በበኩላቸው፤በተያዘው ዓመት በማህበር በመደራጀት በእንቁላል ምርት ላይ በመሰማራት ውጤታማ መሆናቸውን አስረድተዋል።   ከተማ አስተዳደሩ እያደረገ ባለው የመስሪያ ቦታ ድጋፍን ጨምሮ የክትትልና ድጋፍ ስራዎች ለውጤታማነታቸው ጉልህ ድርሻ እንዳለው ነው ያመለከቱት።
አስተዳደሩ ለልማት ተነሺዎች ያስገነባቸውን የመኖሪያ ቤቶች አስረከበ
Jul 4, 2026 178
ጅማ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦የጅማ ከተማ አስተዳደር ለልማት ተነሺዎች ያስገነባውን 300 መኖሪያ ቤቶች አስረከበ። በመኖሪያ ቤቶቹ የርክክብ ስነስርዓት ላይ የክልል እና የዞን እንዲሁም የከተማ አስተዳደሩ የሥራ አመራሮች ተገኝተዋል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ በክልሉ በርካቶችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ይገኛሉ።   ለዚህም በከተማ ብቻ ሳይሆን በገጠር የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ሥራዎችም ምሳሌ ይሆናሉ ብለዋል። ህዝብን ተጠቃሚ ለማድረግ የተቀረጹ ኢኒሼቲቮች እየተተገበሩ ይገኛሉ ያሉት አቶ ጌቱ ፣ በግብርና ዘርፍ፣ በመሠረተ ልማት እና በሌሎችም የልማት ሥራዎች ስኬታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አመልክተዋል። ለኮሪደር ልማት ማህበረሰቡ እያደረገው ያለው ትብብር የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው፣ ሁሉም ልማቶች ለህዝብና ለሀገር ፋይዳቸው የጎላ በመሆናቸው ይጠናከራሉ ብለዋል፡፡   በተለይ በገጠር እና በከተማ ህዝብን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የጅማ ከተማ ከንቲባ ጠሀ ቀመር፤ በከተማው በርካታ ፕሮጀክቶች በመንግስት እየተከናወኑ እንደሆኑና የተጠናቀቁትም ለአገልግሎት ክፍት እየተደረጉ ይገኛሉ ብለዋል።   በከተማዋ በዚህ አመት 80 የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን ጠቅሰው ዛሬ ለልማት ተነሺዎች ተገንብተው የተላለፉ መኖሪያ ቤቶች የዚሁ አንድ አካል ናቸው ብለዋል። እነዚህ መኖሪያ ቤቶች ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው ሲሆን ለ300 አባወራዎች ተላልፈዋል ብለዋል። ከዚህን ቀደም በጅሬን፣ በቆፌ እና በሌሎችም የከተማዋ ቀበሌዎች የተገነቡ የተለያዩ መኖሪያ ቤቶች ለነዋሪዎች መሰጠታቸውንም አስታውሰዋል። ዛሬ የመኖሪያ ቤት ከተሰጣቸው የልማት ተነሺዎች መካከል ሀጂ ሻፊ አባ ጉምቡል፤ የከተማ አስተዳደሩ በገባው ቃል መሠረት ምቹ የመኖሪያ ቤት ስላገኘን ደስተኞች ነን ብለዋል።   ወደፊትም ከመንግስት ጋር በመሆን ለልማት ሥራዎች የሚያደርጉትን ትብብር አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል።
በዞኑ የግብርናውን ዘርፍ በሜካናይዜሽን በመደገፍ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ ትልቅ ለውጥ እየታየ ነው
Jul 4, 2026 286
ሮቤ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በባሌ ዞን የግብርናውን ዘርፍ በሜካናይዜሽን በመደገፍ የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ረገድ ትልቅ ለውጥ እየታየ መሆኑን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሀኪም አልይ አመለከቱ። አርሶ አደሩ የተሻሻሉ አሰራሮችና ቴክኖሎጂዎችን የመጠቀም ዝንባሌና ተግባር እየተሻሻለ መምጣት ለምርትና ምርታማነቱ ማደግ ተጠቃሽ መሆኑ ተመላክቷል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አብዱልሀኪም አልይ በተለይ ለኢዜአ እንዳሉት ፤መንግስት የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት በማሻሻል የምግብ ዋስትናውን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ ነው።   ለአብነትም በበልግ እርሻ ከ256 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት ላይ የተሻሻሉ የግብርና አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ በተለያዩ የሰብል ዘሮች ማልማት መቻሉን አመልክተዋል። አርሶ አደሩ የግብርና ሜካናይዜሽንና ሌሎች የተሻሻሉ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ 80 በመቶ የሚሆነውን መሬት ማልማት መቻላቸውን አመልክተዋል። በአሁኑ ወቅት የአርሶ አደሩ የሜካናይዜሽንና የቴክኖሎጂ አጠቃቀሙ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ መምጣቱን ነው የጠቆሙት። ይሕም በአንድ ሄክታር መሬት የስንዴ ማሳ በአማካይ ይመረት የነበረውን ከ20 ኩንታል የማይበልጥ ምርት ከ60 እስከ 70 ኩንታል ማምረት እንደተቻለም ነው የገለጹት። ለምርትና ምርታማነት መጨመር ዋነኛው ምክንያት የግብርና ሜካናይዜሽንን በማስፋት የተከናወኑ ተግባራት ትልቁን ፋይዳ ማበርከታቸውን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም የዞኑ አርሶ አደሮች ትራክተርን ጨምሮ ሌሎች የግብርና ማሽነሪዎችን በብድር እንኳ ማግኘት ያዳግታቸው እንደነበር ነው ያስታወቁት፡፡ በአሁኑ ወቅት ግን አርሶ አደሩ የግብርና ማሽነሪዎችን ከቀረጥ ነጻ በብድር እንዲያገኝ መንግስት ከፍተኛ ስራ መስራቱን አስተዳዳሪው ተናግረዋል፡፡   በዞኑ በዝናብ ብቻ ሁለት ጊዜ የማምረት ፀጋ መኖሩን ጠቅሰው፤ ከበልግ በተጨማሪ በመኽሩ የምርት ወቅት ከ538 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት በተለያዩ የሰብል ዘሮች የማልማት አቅም መፈጠሩን አክለዋል። ከዚህም ከ17 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት የመሰብሰብ አቅም መፈጠሩን ገልፀዋል። በዞኑ በዝናብ ውኃ ከሚለማው እርሻ ባሻገር የተለያዩ የውኃ አማራጮችን በመጠቀም ከ170 ሺህ ሄክታር መሬት በመስኖ አማራጭ ማልማት መቻሉን ጠቁመዋል። ከ 6 ሚሊዮን ኩንታል ባላይ ምርት መሰብሰብ እንደተቻለም ነው ዋና አስተዳዳሪው የገለጹት። የአርሶ አደሩን የግብርና ሜካናይዜሽንና ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይበልጥ በማሻሻል ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የኢትዮጵያን የግብርና ምርታማነት ወደ አዲስ ምእራፍ ለማሸጋገር ለሚደረገው ሀገራዊ ግብ ስኬት ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግም ነው የተናገሩት።
በጎንደር ከተማ የሚገኙ የመስህብ ሃብቶችን ከጎበኙ ቱሪስቶች 17 ሚሊዮን ብር ገቢ ተገኝቷል
Jul 4, 2026 156
ጎንደር፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በበጀት ዓመቱ በጎንደር ከተማ የሚገኙ የመስህብ ሃብቶችን ከጎበኙ ቱሪስቶች 17 ሚሊዮን ብር ገቢ መገኘቱን የከተማ አስተዳደሩ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ አስታወቀ። የጎንደር ከተማ አስተዳደር የቅርስ ጥበቃና የቱሪዝም ልማት ቡድን መሪ አይቸው አዲሱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተማዋ ለቅርሶች እድሳት መደረጉና የኮሪደር ልማት መካሔዱ ጎብኝዎችን ለመሳብ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል።   በዋናነት የፋሲል አብያተ መንግስታት ላይ የተካሄደው ጥገናና እድሳት፣ በኮሪደር ልማቱ የተገነቡ የመዝናኛ ስፍራዎች፣ የአረንጓዴና ሌሎች የልማት ስራዎች የቱሪስት ፍሰቱ እንዲጨምር ካደረጉ ምክንያቶች መካከል ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ በከተማዋ የሚገኙ የመስህብ ሃብቶችን ከጎበኙ 43 ሺህ 365 የውጭና የሃገር ውስጥ ቱሪስቶች 17 ሚሊዮን ብር ገቢ ማግኘት መቻሉን ተናግረዋል። ከጎብኝዎች ውስጥም ስድስት ሺህ 420 የሚሆኑት የውጭ አገራት ቱሪስቶች ሲሆኑ ቀሪዎቹ የአገር ውስጥ መሆናቸውን አመልክተዋል። በቱሪዝም ልማቱ ከ120 በላይ ፎቶ አንሺዎችና አስጎብኚዎች በተጨማሪ 380 ለሚሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር የኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ መቻሉን አብራርተዋል። የቱሪስቶችን ደህንነትና ምቾት በመጠበቅ የቆይታ ጊዜያቸውን የበለጠ ለማራዘም ከትራንስፖርት፣ ሆቴሎችና አስጎብኝ ድርጅቶች ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በቀጣይም ቅርሶች በመንከባከብ፣ በመጠበቅ ፣ በማልማትና በማስተዋወቅ በርካታ ቱሪስቶችን ለመሳብ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋገጠዋል። የጎንደር ከተማ አስተዳደር አስጎብኚዎች ማህበር ፀሐፊ ሙሉቀን ተገኘ በበኩላቸው ፤ከለውጡ ዓመታት በፊት በጎንደር ከተማ ቅርሶች በአስጊ ሁኔታ ላይ በመገኘታቸው ለጎብኝዎች ዝግ ሆነው መቆየታቸውን አስታውሰዋል። በከተማዋ የሚገኙ አብያተ መንግስታትና ሌሎች ቅርሶች ተጠግነውና ታድሰው ለአገልግሎት ክፍት እንዲሆኑ መደረጉ የጎብኝዎች ቁጥር እንዲጨምር እያደረገ መሆኑን ነው ያነሱት።   በተለይ በጎብኝዎች ይነሱ የነበሩ የመጸዳጃ ቤት፣ የንፁህ መጠጥ ውሃ፣ የመብራትና ሌሎች መሠረታዊ ችግሮች በመሟላታቸው የጎብኚዎችን የቆይታ ጊዜ ለማራዘም እያስቻለ መሆኑን አብራርተዋል። የተገኘው ለውጥም ለአስጎብኚዎችና በተለያዩ የአገልግሎት ዘርፎች ለተሰማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማሳደግ እንዳስቻለም አስረድተዋል። ሌላኛው አስጎብኝ ሳለጌታ ነጋ በበኩሉ፤ የፋሲል አብያተ መንግስታትንና በከተማዋ የሚገኙ ቅርሶች ታሪካዊ ይዘታቸውን ጠብቀው መታደሳቸው የጎብኚዎችን ቀልብ መሳብ አስችሏል ብለዋል። የሀገሪቱን የቱሪዝም ዘርፍ በማሳደግ በኢኮኖሚ ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆንም የኢትዮጵያ አየር መንገድና የቱሪዝም ዘርፍ አካላት በቅንጅት መስራት እንደሚገባቸው አሳስበዋል።
የግንባታ ፕሮጀክቶችን በዲጂታል አሠራር ቁጥጥርና ክትትል ማድረግ የሚያስችል ሥርዓት ወደ ሙሉ ትግበራ ገብቷል
Jul 4, 2026 114
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ባለሥልጣን የግንባታ ፕሮጀክቶችን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ቁጥጥርና ክትትል ማድረግ የሚያስችል ሥርዓት ሙሉ ለሙሉ ወደ ሥራ ማስገባቱን ገለጸ። በዲጂታል 2030 ስትራቴጂ መሠረት የፕሮጀክቶችን አፈጻጸምና አስተዳደር በዲጂታል ሥርዓት ሙሉ በሙሉ የመከታተል ግብን ለማሳካት ባለሥልጣኑ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር (ኢንሳ) ጋር በመተባበርም "ኮንስትራክሽን ሬጉላተሪ ኢንፎርሜሽን ሲስተም" የተሰኘ የዲጂታል ሥርዓት አልምቷል። የባለሥልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ምዑዝ በድሩ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪውን ለማዘመን ሰፋፊ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው። በተለይም ዘርፉን በቴክኖሎጂ የተደገፈና ቀልጣፋ ለማድረግ የዲጂታላይዜሽን ሥርዓት መዘርጋት ወሳኝ መሆኑን የጠቀሱት ኢንጂነር ምዑዝ፤ በአሁኑ ወቅት የዲጂታል አሠራርን ሙሉ ለሙሉ ለመተግበር ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። ባለሥልጣኑ ፕሮጀክቶችን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ክትትል ማድረግ የሚያስችል "ኮንስትራክሽን ሬጉላተሪ ኢንፎርሜሽን ሲስተም" የተሰኘ ሥርዓት ከኢንሳ ጋር በመተባበር ማልማቱንም ጠቅሰዋል። ይህ የዲጂታል ሥርዓት በሙከራ ደረጃ ተተግብሮ ውጤታማ መሆኑን በማንሳት፣ አሁን ላይ ወደ ሙሉ ትግበራ እየገባ መሆኑን አብራርተዋል። ይህም የግንባታዎችን ጥራትና ፍጥነት በአግባቡ በመከታተል የኮንስትራክሽን ዘርፉን ውጤታማነት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋግረዋል ብለዋል። ይህ የቁጥጥር ሥርዓት የሕንጻ ግንባታዎችን ብቻ ሳይሆን፣ ከፈቃድ አሰጣጥ ጀምሮ የፕሮጀክትና የግብዓት ቁጥጥርን እንዲሁም አጠቃላይ የፕሮጀክቶችን አፈጻጸም በዲጂታል መንገድ ለመከታተል የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። የአሠራር ሥርዓቱ ማንኛውም የኮንስትራክሽን ፕሮጀክት በተቀመጠለት ጊዜ፣ በጀትና ጥራት ተጠናቆ ለአገልግሎት እንዲበቃ በቴክኖሎጂ የታገዘ ጥብቅ ክትትል ማድረግ እንደሚያስችልም ጠቁመዋል። ሥርዓቱ ተቆጣጣሪ ባለሙያዎች ቢሮ ሆነው የትኞቹ ፕሮጀክቶች የት ቦታ ላይ እንደሚገኙና በምን ዓይነት የግንባታ ደረጃ ላይ እንዳሉ በቀላሉ ለመከታተል ያስችላቸዋል ብለዋል። በኮንስትራክሽን ዘርፉ ይስተዋሉ የነበሩ ሀሰተኛ ሰነዶችን ጥቅም ላይ የማዋል ሕገ-ወጥ ድርጊቶችን ጨምሮ፣ ብልሹ አሠራሮችን በማስቀረት ረገድ የቴክኖሎጂው ወደ ሥራ መግባት ትልቅ ለውጥ እንደሚያመጣ አመልክተዋል። ግልጽነትን በመፍጠር ረገድም አዲስ ምዕራፍ እንደሚከፍት የገለጹት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፤ ዘርፉን ከቢሮክራሲ ማነቆዎች በማላቀቅ የኢንቨስትመንት ከባቢውን እንደሚያሳልጥም አብራርተዋል። በፈቃድ አሰጣጥ ሂደት ላይ የዲጂታላይዜሽን ሥራ በስፋትና በትኩረት እየተከናወነ ይገኛል ያሉት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፤ ይህም ወደ ተሟላ የዲጂታል ትግበራ ምዕራፍ እንድንሻገር ጠንካራ መሠረት ጥሏል ነው ያሉት። ሥርዓቱ በዲጂታል 2030 ስትራቴጂ መሠረት የኢትዮጵያን የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ፣ ቀልጣፋና ተወዳዳሪ ለማድረግ የተጀመረውን ጉዞ እንደሚያፋጥንም ጠቅሰዋል። የፕሮጀክት ማኔጅመንት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ታምራት ሙሉ በበኩላቸው፤ ኢንስቲትዩቱ የሚሰጣቸውን ሥልጠናዎች ወደ ዲጂታል ለማሸጋገር በትኩረት እየሠራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በዚህም መሠረት ስድስት የሚሆኑ የሥልጠና መስኮችን በቨርቹዋል (በበይነ-መረብ) መስጠት መጀመሩን ጠቁመዋል። በኮንስትራክሽን ዲዛይን ዘርፍ ያለውን ክፍተት መቅረፍ የሚያስችል የዲጂታል ቴክኖሎጂ መዘርጋቱንም ኢንጂነር ታምራት ገልጸዋል። ይህ የዲዛይን ቴክኖሎጂ ወይም Building Information Modeling (BIM) የተሰኘው ሥርዓት፤ ሕንጻው በአካል ከመገንባቱ በፊት በዲጂታል መድረክ ላይ ቀድሞ ታይቶ እንዲሠራ የሚያደርግ መሆኑንና ይህም የግንባታ ጥራትን በከፍተኛ ደረጃ ለማስጠበቅ እንደሚያስችል አብራርተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም