ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በማምረት ክብራችንን እና ነፃነታችንን በማስከበር ዕድገትን ማምጣት ይጠበቅብናል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) 
May 3, 2026 54
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያዊያን በማምረት ክብራችንንና ነፃነታችንን በማስከበር ዕድገትን ማምጣት ይጠበቅብናል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 25 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ መርቀው ከፍተዋል። ለአራተኛ ጊዜ "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በተዘጋጀው ኤክስፖ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ቴዎድሮስ ምኅረት፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ማምረት ሉዓላዊነትን ያጎናፅፋል፣ አለማምረት ደግሞ ታሪክን ያጎድፋል ብለዋል። ለአብነትም ኢትዮጵያ ፀጋዎቿን አልምታ ባለመጠቀሟ በዓለም አቀፋዊ ወቅታዊ ሁኔታ ሳቢያ ተግዳሮት ገጥሟት እንደነበር አውስተው፤ በዚህም በሁሉም መስክ ማምረት የተሟላ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥ ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን ታሳቢ በማድረግ አበክሮ መሥራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። አብዛኛውን ፍላጎቱን በገቢ ምርት ላይ ያደረገ ሀገር ነፃና ሉዓላዊ ነኝ ሊል አይችልም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ አምርታ የተሟላ ሉዓላዊነት እንድትጎናጸፍ በኅብረትና በአንድነት በመሥራት ለልጆቻችን ነፃና የተሟላ ሉዓላዊነት የተጎናጸፈችዋን ኢትዮጵያ ዕውን ማድረግ ይጠበቅብናል ብለዋል። የዛሬ አራት ዓመት የተጀመረው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄም የኢንዱስትሪ ዘርፍ ምርታማነት በጥራት፣ በደረጃና በዓይነት እያደገ መምጣቱን እንደሚያሳይ ተናግረዋል። ዘንድሮ የኢትዮጵያን የ10 ነጥብ 2 ዕድገት ለማረጋገጥም የኢንዱስትሪና የኢትዮጵያ ታምርት የሚፈጥሩት ጥምረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አንስተዋል።   ከዓመታት በፊት የወጪ ንግድ ሦስት ቢሊዮን ዶላር ለመሻገር ሲንገዳገድ እንደነበር አስታውሰው፤ ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ 10 ቢሊዮን ዶላር በማሳካት ታላቅ ድል እንደሚሆን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ዘርፍም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ሲጀመር የነበረው የአራት ነጥብ ሰባት ዕድገት አሁን ላይ 10 ነጥብ 7 ዕድገት ማስመዝገቡን አስረድተዋል። ባለፉት አራት ዓመታትም ከውጭ ይገባ የነበረን የ14 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ወጪ በሀገር ውስጥ መተካት እንደተቻለም አስታውቀዋል። በተለያዩ ምክንያቶች ሥራ አቁመው የቆዩ 993 ኢንዱስትሪዎችም መልሰው ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን አንስተዋል። ባለፉት አራት ዓመታትም 3 ሺህ 680 አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉን መቀላቀል እንደቻሉ ጠቅሰዋል። በኢንዱስትሪ ዘርፍ በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በተኪ ምርትና በወጪ ንግድ ዕድገት ገንቢ ሚና እየተወጡ ለሚገኙ የዘርፉ ተዋናዮች ምስጋና አቅርበዋል። በቀጣይም ካላመረትን ክብርና ነፃነታችንን መጎናጸፍ አንችልም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የቴክኒክ ኮሚቴ በማዋቀር ለዘርፉ ዕድገት ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። አራተኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖም የአዲስ አበባ ነዋሪዎች፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች በመጎብኘት ሊያተርፉበት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አራተኛውን 'ኢትዮጵያ ታምርት' ኤክስፖ 2018 በይፋ መርቀው ከፍተዋል
May 3, 2026 37
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን የአምራች ዘርፍ ለማስፋፋት የሚደረገውን ጥረት የሚያጠናክረውን አራተኛውን 'ኢትዮጵያ ታምርት' ኤክስፖ 2018 ዛሬ በይፋ መርቀው ከፍተዋል። ‎‎ኤክስፖው እስካሁን ያሳያቸው እና የተመዘገቡ ዋና ዋና ስኬቶች፦ ‎- የአምራች ዘርፉ ግብዓት አቅርቦት በዓመት ከ9 ሚሊዮን ወደ 15 ሚሊዮን ቶን አድጓል፤ ‎- ለአዳዲስ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንቶች ከ3.4 ጊጋ ዋት በላይ የኤሌክትሪክ ኃይል ቀርቧል፤ ‎- ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች የሚቀርበው የፋይናንስ አቅርቦት ከ8.1 ቢሊዮን ወደ 50 ቢሊዮን ብር ያደገ ሲሆን ለከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች ደግሞ ከ262 ቢሊዮን ብር በላይ ከፍ ብሏል፤ ‎- ለዘርፉ ከ2.28 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ተመድቧል፤ ‎- የፋብሪካዎች የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ አድጓል፤ ‎- የማምረት አቅምና ዕድገት ከ4.8 በመቶ ወደ 10.7 በመቶ ከፍ ያለ ሲሆን፣ በቀጣይም ተጨማሪ ዕድገት ይጠበቃል፤ ‎- ምርትን በሀገር ውስጥ በመተካት እስከ 4.85 ቢሊዮን ዶላር ማዳን የተቻለ ሲሆን የወጪ ንግድም ከፍተኛ እድገት እያሳየ ይገኛል፤ ‎- ከ2,800 በላይ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ የተቻለ ሲሆን፣ ለ1.4 ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል። ‎ ‎ኤክስፖው ኢንዱስትሪዎችን የሚያስተሳስር፣ ኢንቨስትመንትን የሚስብ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ አምራቾችንና በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችን የሚያገናኝ ቁልፍ ሀገራዊ መድረክ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። ‎በአጠቃላይ የኤክስፖው መከፈት የአምራች ዘርፉ ለኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ያለውን ፋይዳ በማጉላት የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ሽግግር እያፋጠነ መሆኑን እንደሚያሳይም ተመላክቷል።
‎በዘንድሮው “ኢትዮጵያ ታምርት” ኤክስፖ ላይ የሀገራዊ ርዕያችንን ተጨባጭ ስኬት መመልከት ትልቅ ክብር ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 3, 2026 88
‎አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦በዘንድሮው “ኢትዮጵያ ታምርት” ኤክስፖ ላይ የሀገራዊ ርዕያችንን ተጨባጭ ስኬት መመልከት ትልቅ ክብር ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የአራት ዓመታት ተከታታይ ጥረት እና የሚጨበጥ ውጤት! በሚል በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ‎በዘንድሮው “ኢትዮጵያ ታምርት” ኤክስፖ ላይ የሀገራዊ ርዕያችንን ተጨባጭ ስኬት መመልከት ትልቅ ክብር ነው ብለዋል።   በውጤት ተኮር አመራራችን ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ የኢንዱስትሪ መስፋፋት ተንጸባርቋል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ ይኸውም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን አማካይ የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ ከፍ በማድረግ፣ ባለፉት አራት አመታት ከ2,800 በላይ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ የተቻለ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ እንዲሁም በ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ በሀገር ውስጥ ተኪ ምርት ከ4.85 ቢሊየን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ በማዳን መረጋገጡን አመላክተዋል።   ኤክስፖው ከመላው የሀገሪቱ የተወጣጡ ንቁ አምራቾችን እና ስታርትአፖችን በጨመረ ዐቅም በአንድነት ማሰባሰቡን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‎በጋራ በመሆን ይህንን ጠንካራ መነቃቃት በማስቀጠል፣ ለሚመጣው ትውልድ ጸኑ፣ በኢንዱስትሪ የበለጸገች እና ራሷን የቻለች ኢትዮጵያን እንገነባለን በማለት መልዕክት አስተላልፈዋል።
አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ውጤት እያስገኙ ነው
May 3, 2026 117
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦አዲስ አበባን እንደስሟ ውብና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን የከተማዋ ቱሪዝም ኮሚሽን አስታወቀ። መንግስት ካለፉት የለውጥ ዓመታት ወዲህ ኢትዮጵያን ተወዳዳሪ የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ ሀብቶችን በመግለጥ፣ በርካታ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎችን በማልማትና በነባሮቹ ላይም እሴት የመጨመር ስራዎችን አከናውኗል። የአፍሪካ ህብረት፣ የበርካታ ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ ድርጅቶች እንዲሁም የኤምባሲዎች መቀመጫ የሆነችውን አዲስ አበባን ስሟን የሚመጥን የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ እና ዘላቂ የቱሪዝም ልማትን ለማረጋገጥ በርካታ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ።   ለውጡን ተከትሎ መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉ የሰጠው ትኩረት እና በተሰሩ የልማት ስራዎች አዲስ አበባ ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን አስችሏታል። ለአብነትም የእንጦጦ፣ አራዳ፣ ወዳጅነት፣ አንድነት ፓርኮች እንዲሁም በከተማዋ መሃልና ዙሪያ ያሉ ተፋሰስ ወንዞችን እና የኮሪደር መሰረተ-ልማቶችን ጨምሮ ሌሎች የአረንጓዴ ልማት ስፍራዎች ይጠቀሳሉ። በዚህም ከተማዋ ያላትን የተፈጥሮ፣ ታሪካዊና ባህላዊ መስህቦች በመጠቀም ረገድ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃንና የአካባቢ ዘላቂነትን ከማረጋገጥ ጋር ተያይዞ ትልልቅ ስራዎች ተሰርተዋል። ይህም አዲስ አበባን ልዩ የኢኮ ቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን፤ ባህልን፣ ታሪክንና ተፈጥሮን አጣምራ የያዘች ልዩ መስህብ አድርጓታል። የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሁንዴ ከበደ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ በለውጡ ዓመታት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ አስደናቂ ተግባራት ተከናውነዋል።   በመዲናዋ በአጭር ጊዜ ውስጥ ጥራትና ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ግንባታዎች ተከናውነው ስራ መጀመራቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም በከተማዋ ያሉ የቱሪዝም መስህብ ስፍራዎችን በማልማት፣ ቅርሶችን በመጠበቅ፣ በማስተዋወቅና የኢኮኖሚ ምንጭ በማድረግ በኩል ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል ሲሉም ተናግረዋል። ከለውጡ ወዲህ በመዲናዋ የተሰሩት የልማት ስራዎች የተለያዩ የቱሪዝም መዳረሻ ቦታዎች እንዲፈጠሩ ማስቻሉን ገልጸው፤ አዲስ አበባን እንደስሟ ውብና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት አስገኝተዋል። ለውጡን ተከትሎም በኮሪደር ልማት ከተማዋን ለኑሮ ምቹ፣ ፅዱና ማራኪ በማድረግ፤ ስሉጥ የእግረኛ፣ የብስክሌትና የተሽከርካሪ መንገዶችን ጨምሮ አረንጓዴ መናፈሻዎች በመገንባታቸው በዘርፉ ላይ እድገት መመዝገብ መቻሉን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ አዲስ ኢንዱስትሪያዊ ስብዕና እና የስራ ባህል እየገነባ ነው
May 3, 2026 144
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ታምርት ከቴክኒካዊ ብቃት ባሻገር፣ አዲስ ኢንዱስትሪያዊ ስብዕና እና የላቀ የሥራ ባህል በመፍጠር ረገድ ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመረው ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ፤ 830 ፋብሪካዎችን ዳግም ወደ ስራ በማስገባት፣ 4 ነጥብ 85 ቢሊየን ዶላር ገቢ ምርትን በመተካት እና 433 ሚሊየን ዶላር ከኤክስፖርት በማስገኘት አስደናቂ የኢንዱስትሪ ሽግግር ውጤት ማስመዝገቡንም አመልክቷል። ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ መንግሥት ንቅናቄውን ሲጀምር ግቡ ምርትን ማሳደግና የውጭ ምንዛሬን መታደግ ብቻ እንዳልነበረ አገልግሎቱ ገልጿል። ከኢኮኖሚያዊ ስሌቶች ባሻገር፣ ትልቁና ስትራቴጂካዊው ስኬት የተመዘገበው ኢትዮጵያን የዕውቀትና የክህሎት ምንጭ በሚያደርገው የሰው ሀብት ልማት ላይ መሆኑ ተመላክቷል። ዛሬ ላይ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ የፋብሪካዎች ስብስብ መሆኑ ቀርቶ፣ የነገዋን ኢትዮጵያ የሚገነቡ ብቁ ባለሙያዎችና መሪዎች የሚፈሩበት ታላቅ የተግባር ትምህርት ቤት መሆን ችሏል። ይህ ሽግግር ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተወዳዳሪነት ከጥሬ ዕቃ ላኪነት ወደ ቴክኖሎጂ ላኪነትና ክህሎት አቅራቢነት ከፍ የሚያደርግ ለነገዋ ኢትዮጵያዊ መሠረት የሚጥል የታሪካችን እጥፋት መሆኑን ነው አገልግሎቱ ያስታወቀው። በታላላቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች፣ በኢንዱስትሪ ፓርኮችና በግዙፍ ፋብሪካዎች ውስጥ የታየው ተጨባጭ ለውጥ የመንግሥትን የፖሊሲ ጥንካሬ በተግባር የሚያረጋግጥ ነው ተብሏል። ከዚህ ቀደም በከፍተኛ ክፍያ በሚመጡ የውጭ ሀገር ዜጎች ብቻ ይተዳደሩ የነበሩ ውስብስብ የቴክኖሎጂ ሲስተሞች፣ ዘመናዊ የምርት መስመሮችና የሶፍትዌር መሠረተ-ልማቶች ዛሬ ላይ ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ ወጣት መሐንዲሶችና ቴክኒሻኖች እየተመሩ ይገኛሉ። ይህ ስኬታማ የዕውቀት ሽግግር፣ መንግሥት ጥራት ያለው ፖሊሲ የመቅረጽ ብቻ ሳይሆን ፖሊሲን በተጨባጭ ወደ ተግባር የመለወጥና የማስፈጸም አቅም እንዳለው ትልቅ ማሳያ መሆኑ በመረጃው ላይ ተብራርቷል። በዘርፉ የተሠማሩ ኢትዮጵያውያን ወጣቶችም የተፈጠረላቸውን ምቹ ዐውድ ተጠቅመው ቴክኖሎጂን የመቀበል ብቻ ሳይሆን፣ የመግራትና የማላመድ ብቃታቸውን በተግባር እያሳዩ ይገኛሉ። በዚህም ኢትዮጵያ ለዘመናት የነበረባትን የቴክኖሎጂ ጥገኝነት በፈጠራ አቅማቸው እያስቀሩና አዳዲስ የሥራ ባሕልና የታሪክ ምዕራፍ እየጻፉ መሆኑን አገልግሎቱ ገልጿል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከቴክኒካዊ ብቃት ባሻገር፣ አዲስ ኢንዱስትሪያዊ ሰብዕና እና የሥራ ባህል እየገነባ ይገኛል። በዘርፉ የተሰማሩ ዜጎች ዓለም አቀፍ የጥራት ቁጥጥር ስታንዳርዶችን፣ ጥብቅ የጊዜ አጠቃቀምንና ስልታዊ የአመራር ክህሎትን በመላበስ ላይ ናቸው። ከታችኛው የሥራ እርከን ተነስተው በዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ውስጥ እስከ ከፍተኛ የውሳኔ ሰጪነት ደረጃ የደረሱ ወጣቶች፣ ኢትዮጵያ ለዓለም ገበያ የምታቀርበው "ምርጥ ምርት" የሰው ሀብቷ መሆኑን እያስመሰከሩ መሆኑ ተጠቁሟል። መንግሥት የኢንዱስትሪ ሽግግሩን ትክክለኛ ፍሬ የሚለካው በወጪ ንግድ ስሌቶች ብቻ ሳይሆን በቴክኖሎጂ የደረጀና በዕውቀት የበለጸገ አምራች ዜጋ መፈጠሩ መሆኑን አገልግሎቱ አስታውቋል። በመሆኑም ይህን የክህሎት አብዮት ይበልጥ በማፋጠንና ዘርፉን የቴክኖሎጂ ምንጭ በማድረግ፣ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎች በቁርጠኝነት እንደሚቀጥሉም ገልጿል።
ተፈጥሯዊና የባህል ሀብቶችን ለቱሪዝም ልማት ለማዋል የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው 
May 2, 2026 216
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ የተፈጥሯዊና የባህል ሀብቶችን ለቱሪዝም ልማት ለማዋል የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ተመላከተ። "በኢትዮጵያ ዘመናዊ ቱሪዝም ልማት ውስጥ ፈጠራና ዘላቂነት" በሚል መሪ ሀሳብ ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮጵያ ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 15ኛው ሀገር አቀፍ የምርምር ኮንፍረንስ ተካሂዷል።   በኮንፈረንሱ የዩኒቨርሲቲው ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ችሮታው አየለ (ዶ/ር) እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው በቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ የትምህርት መስክ ተማሪዎችን ከማሰልጠን ባለፈ የጥናትና ምርምር ሥራዎችን በማድረግ ዘርፉ ለሀገር እድገት ያለውን ፋይዳ ለማሳደግ የበኩሉን እየተወጣ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በተጀመረው ገበታ ለሀገርና ገበታ ለትወልድ መርሀ ግብር በርካታ የመስህብ ስፍራዎች መልማታቸውን የማልማት ሥራ መሰራቱን ለማሳያነት ጠቅሰዋል። በቀጣይም ተፈጥሯዊና የባህል ሀብቶችን ለቱሪዝም ልማት ለማዋል የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸውም አክለዋል።   የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ነጋሽ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የሆቴልና ቱሪዝም ዘርፉ በዓለማችን እጅግ ከፍተኛ ትኩረት እያገኙ ከመጡ የሥራ መስኮች አንዱ ነው። በአትዮጵያ በርካታ የመስህብ ሥፍራዎች ቢኖሩም አልምቶ ከመጠቀም እንጻር ተግዳሮቶች እንደነበሩ አስታውሰው፣ በለውጡ መንግስት የመዳረሻ ስፍራዎችን በማስፋፋት ኢትዮጵያ ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን ተሰርቷል ብለዋል።   የኢትዮጵያ ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተርና በኮንፈረንሱ ጥናት ያቀረቡት ይታሰብ ስዩም፣ በዘመናዊ የቱሪዝም ልማት ውስጥ አዳዲስ ፈጠራና ዘላቂነትን መሰረት ያደረገ የማልማትና ማስተዋወቅ ሥራ መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። የቱሪዝም መሰረተ ልማትን ከቴክኖሎጂ ጋር የማስተሳሰርና አገልግሎቱን ማዘመን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ፋይዳውን ከማሳደግ ባለፈ ሀብቱ ለትውልድ እንዲተላለፍ ያግዛል ብለዋል።   በስነምህዳር ቱሪዝም (ኢኮ ቱሪዝም) ዙሪያ የምርምር ሥራቸውን ያቀረቡት በቦረና ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ ጸለፎ ጫካ፣ በሀገራችን ቱሪዝምን ከስነምህዳር ጋር በማስተሳሰር እየተሰራ ያለው ሥራ በርካታ ጎብኚዎችን እየሳበ መሆኑን ገልጸዋል። የመዳረሻ ልማት ሥራዎች የአካባቢውን ማህበረሰብ፣ ባህል፣ አኗኗር እና አረንጓዴ አሻራን ያስተሳሰረ በመሆኑ ትልቅ ፋይዳ እንዳለውና በከተሞች የተጀመረውን የቱሪዝም መሰረተ ልማት ተደራሽነት ወደ ሌሎች ማስፋፋት እንደሚገባ ጠቁመዋል። በመድረኩ ከቱሪዝም ጋር የተያያዙ ጥናታዊ የምርምር ሥራዎች የቀረቡ ሲሆን ከሀዋሳና ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች የተወከሉ ምሁራን፣ የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት መምህራንና በቱሪዝም ዘርፍ የተሰማሩ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
በዞኑ በመኸር እርሻ በዘር ከሚሸፈነው መሬት ከግማሽ በላይ የሚሆነው በኩታ ገጠም የሚለማ ነው
May 2, 2026 132
ደሴ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን በመጪው የመኸር እርሻ በዘር ከሚሸፈነው 432 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆነው በኩታ ገጠም እንደሚለማ የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። አስተዳደሩ የ2018/19 መኸር ምርት ዘመን የሰብል ልማት ንቅናቄ መድረክ ዛሬ በደሴ ከተማ አካሂዷል።   የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ አሊ ይማም በመድረኩ እንደገለጹት፣ የመኸር እርሻ በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት የተያዘውን ግብ የሚሳካበት ነው። በመኸር እርሻ ከሚለማው 432 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ከ249 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በኩታገጠም እንደሚለማ ገልጸዋል። በአጠቃላይ ለመሰብሰብ ከታቀደው ከ16 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ከ10 ነጥብ 6 ሚሊየን ኩንታል በላይ የሚሆነው በኩታ ገጠም ከሚለማው ሰብል እንደሚሰበሰብ አስታውቀዋል። በልማቱ ምርታማነትን ለማሳደግ የግብርና ቴክኖሎጂና አዳዲስ አሰራሮችን እንዲሁም ግብዓትን በአግባቡ መጠቀም ላይ አቅጣጫ ተቀምጦ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።   የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው በመኸሩ የታቀደውን ምርት ለማግኘት ለአርሶ አደሩ የተጠናከረ ድጋፍና ክትትል ይደረጋል ብለዋል። በተለይም የሜካናይዜሽን እርሻ ላይ በማተኮርና የተሻሻሉ የግብርና አሰራርና ቴክኖሎጂዎችን በመተግበር የምርት ዕድገትን ለማረጋገጥ ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል።
በክልሉ የሚገኙ የልማት ድርጅቶች ልማትን ለማስቀጠል ያላቸውን እቅም እንዲያጠናክሩ እየተሰራ ነው
May 2, 2026 126
ባህርዳር፤ ሚያዚያ 24/2018 (ኢዜአ)፦ የልማት ድርጅቶች በክልሉ እድገት ውስጥ ያላቸውን አበርክቶ እንዲያጠናክሩ እየተሰራ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአማራ ክልል ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) ገለጹ። በአማራ ልማት ማህበር (አልማ) የተቋቋመው አልማኮን የህንጻ ኮንስትራክሽን ተቋራጭ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ዛሬ ማምሻውን አዲስ ብራንዱ ይፋ ተደርጓል። የአማራ ክልል ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ በክልሉ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ልማትን ለማሳደግ የአጋር አካላት ተሳትፎ የጎላ ሚና እያበረከተ ነው። በመሰረተ ልማት ግንባታና ማህበራዊ ልማት ላይ በመሳተፍም የህዝብ ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ አጋር አካላቱ እገዛ እያደረጉ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዚሁ ማሳያ የሆነው አልማኮን በአዲስ ብራንድ መምጣቱ የተሰጠውን ተልእኮ በብቃት በመፈጸም የክልሉን እድገት ለማፋጠንና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የበኩሉን ድርሻ ይብልጥ እንዲያጠናክር ያደርገዋል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም በክልል የሚገኙ የልማት ድርጅቶች በክልሉ እድገት ውስጥ ያላቸውን አበርክቶ እንዲያጠናክሩም ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ነው የገለጹት። የአማራ ልማት ማህበር /አልማ/ ዋና ስራ አስፈጻሚና የአልማኮን ዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ መላኩ ፈንታ በበኩላቸው ፤ ማህበሩ ሀብት የሚያመነጩ ተቋማትን በማቋቋም ከእርዳታ ጠባቂነት ለመውጣት እየሰራ ይገኛል። አልማኮን የተሰኝው ተቋምም በኮንስትራክሽን፣ በሪል እስቴት ልማትና በግንባታ ግብዓት አቅርቦት ላይ እየሰራ እንደሚገኝም ነው ያመለከቱት። ኩባንያው በአዲስ ብራንድ መምጣቱም በኮንስታራክሽንና በኢንዱስትሪው ዘርፍ ተወዳዳሪ ምርቶችን ይዞ ወደ ገበያ በመግባት የክልሉን እድገት ለፋጠን የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት እንደሚያስችለው አስረድተዋል። የአልማኮን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሰጥቷል ደሳለኝ እንደገለጹት፤ ኩባንያው በ2005 ጀምሮ በኮንስትራክሽን ዘርፉ በመሰማራት ለክልሉ እድገትና ለህዝቡ ተጠቃሚነት የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ኩባንያው አዲስ ብራንድ ይዞ መምጣቱም በአምስት ዓመት ስትራቴጅክ እቅዱ መሰረት አዲስ አደረጃጀትና አሰራር በመፍጠር የገበያ አድማሱን ለማስፋት እንደሚያስችለው አስገንዝበዋል። በመደረኩ ላይም በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ዘርፍ አስተባባሪ ድረሥ ሳህሉ(ዶ/ር)ን ጨምሮ ሌሎች የክልሉ የቢሮ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።    
የመምህራንን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት የክልሉ መንግስት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ ያደርጋል
May 2, 2026 250
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ የመምህራንን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት የክልሉ መንግስት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ እንደሚያደርግ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለፁ፡፡ ‎አቶ ደስታ ሌዳሞ የክልሉ መምህራን ማህበር ለሚያስገነባቸው የመምህራን ሆስፒታል እና ሁለገብ ሕንጻዎች ግንባታ ሥራ የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል፡፡   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት መምህራን በክልሉ ሁለንተናዊ ዕድገት ላይ ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑንና በተለይ ከማህበሩ ጋር በመቀራረብ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የትምህርት ሥብራትን ለመጠገንና የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ እየተደረገ ባለው ጥረት ተጨባጭ ለውጥ እየታየ መምጣቱንም ተናግረዋል፡፡ የክልሉ መንግስት ለግንባታ ሥራው ማስጀመሪያ የሚሆን 50 ሚሊየን ብር ድጋፍ ማድረጉንና ሕንፃው ተጠናቆ ለአገልግሎት እስኪበቃ የክልሉ መንግስት ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡   የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንት ዮሐንስ በንቲ (ዶ/ር) በበኩላቸው መምህራን በትውልድ ግንባታ ውስጥ ተሳትፏቸው ከፍተኛ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ የመምህራን ኢኮኖሚያዊ አቅም እንዲሻሻል፣ ምቹ የሥራ አካባቢ እንዲኖራቸውና ጤናቸው በአግባቡ ተጠብቆ በበለጠ ትጋት እንዲሰሩ ለማስቻል ማህበሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ ፕሮጀክት ቀርጾ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   የሲዳማ ክልል መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንት ኢያሱ ፍቅሬ የክልሉ መምህራን ጠንካራ የትምህርት ሥርዓትን ለመገንባትና የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ከመንግስት ጋር በቅንጅት እየሰሩ ይገኛሉ ብለዋል። ማህበሩ ከ46 ሺህ በላይ አባላትን በሥሩ መያዙን ጠቁመው የመምህራን መታከሚያ ሆስፒታልና ሁለገብ ሕንጻዎቹ የረጅም ጊዜ ጥያቄ ሆነው መቆየታቸውን አስታውሰዋል፡፡ በክልሉ በየደረጃው በመንግስት እየተደረገላቸው ላለው ያልተቋረጠ ድጋፍ አመስግነው የማህበሩ አባላት ትውልድ የመቅረጽ ሀላፊነታቸውን በበለጠ ተናሳሽነትና ትጋት አጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። ለመምህራን ሆስፒታል የሚገነባው ሕንጻ ባለ 6 ወለል መሆኑን ገልጸው፣ ሁለገብ ሕንጻው ባለ 12 ፎቅ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሕንጻዎቹ በ1ሺህ 200 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ እንደሚያርፉ ገልጸው ለግንባታቸውም በአጠቃላይ ከ900 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ እንደሚጠይቁ ገልጸዋል።
አርሶ አደሮች ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በወቅቱ መቅረቡ ለግብርና ሥራቸው ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን ተናገሩ
May 2, 2026 80
ወልቂጤ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ለበልግ ወቅት አዝመራ የአፈር ማዳበሪያ እና ምርጥ ዘር በወቅቱ ማግኘታቸው ለግብርና ሥራቸው ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን ኢዜአ ያነጋገራቸው የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ።   የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ወቅቱን ጠብቆ መቅረቡ ለግብርና ልማት ሥራቸው መሳካት ከፍተኛ ዐቅም መፍጠሩን የአበሽጌ ወረዳ አርሶ አደር ሰብስቤ ወልደሃዋርያት ተናግረዋል። ከአራት ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ማግኘታቸውን ገልጸው፤ እስካሁንም ሦስት ሄክታር መሬታቸውን በበቆሎ እና በማሽላ ምርጥ ዘር መሸፈናቸውን አስረድተዋል።   አርሶ አደር ፍቃደ ተበቃም የቀረበላቸውን የአፈር ማዳበሪያ ተጠቅመው ማሳቸውን በበቆሎ ዘር እንደሸፈኑ ገልጸዋል።   በዞኑ ከ82 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበልግ አዝመራ በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አበራ ወንድሙ ናቸው። በበልግ እርሻ በቆሎ፣ ማሽላ፣ ድንችና ሌሎች ሰብሎች እንደሚለሙ ጠቅሰው፤ እስካሁን 34 ሺህ ሄክታር ማሳ በድንች ዘር መሸፈኑን አረጋግጠዋል። በ46 ሺህ ሄክታር ላይ በቆሎ እንደሚለማ ጠቁመው፤ በግንባር ቀደም አርሶ አደሮችም በሄክታር ከ121 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ግብ ተጥሏል ብለዋል። የበልግ አዝመራ ልማቱን ለማሳካት 8 ሺህ 200 ኩንታል የበቆሎ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ ቀመቅረቡን ጠቁመዋል። ከሰው ሠራሽ ማዳበሪያ በተጨማሪ የተፈጥሮ ማዳበሪያ (ኮምፖስት) ተዘጋጅቶ ለግብርና ሥራው ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
መንግሥት ሀገራዊ ብልፅግናን የሚያፋጥኑ መዋቅራዊ ለውጦችን በስኬት እያከናወነ ይገኛል -የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
May 2, 2026 80
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 24/2018 (ኢዜአ)፦ መንግሥት ዘላቂ አጀንዳዎች ላይ በማተኮር ሀገራዊ ብልፅግናን የሚያፋጥኑ መዋቅራዊ ለውጦችን በስኬት እያከናወነ እንደሚገኝ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለጸ። አገልግሎቱ ባወጣው መግለጫ፤ መንግሥት የ'ዲጂታል ኢትዮጵያ'ን መነሻ ያደረገውና ግልጽነትን ያሰፈነው ዘመናዊ የመንግሥት አገልግሎት ሥርዓት በተግባር ፍሬ እያፈራ ያለ ታላቅ ሀገራዊ ሽግግር ነው ብሏል። በተለይም የቴሌኮም ዘርፍ ሊበራላይዜሽን ርምጃዎች የውድድር መንፈስን በመፍጠር የኢንተርኔትና የዲጂታል ትስስር ተደራሽነትን በከፍተኛ ፍጥነት ማሳደግ መቻሉን አመልክቷል። ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ፍትህን ለማስፈን ወሳኝ የሆነው የ"ፋይዳ" ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ ሥርዓትም በተሳካ ሁኔታ በመተግበር ላይ ይገኛልም ነው ያለው። ይህ ሥርዓት በአጭር ጊዜ ውስጥ በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ የፋይናንስ አካታችነትን ከማረጋገጡም በላይ የመንግሥትን ሀብት ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ለማከፋፈል እና ድጋፍ ለሚሹ የሕብረተሰብ ክፍሎች በቀጥታ እንዲደርስ በማድረግ ረገድ የላቀ አስተዋፅዖ የሚያበረክት ዳግማዊ ሕዳሴያችን ነው ሲልም አብራርቷል። የዜጎችን እንግልት ለማስቀረት እና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን የመንግሥት አገልግሎቶችን ወደ ዲጂታል አማራጭ የማሸጋገሩ ጥረት ሌላው ተጨባጭ ስኬት የተመዘገበበት መስክ ነው ያለው መግለጫው፤ የተለያዩ የሚኒስቴሮች የፌዴራል ተቋማት አገልግሎቶቻቸውን በኤሌክትሮኒክስ መንገዶች መስጠት በመጀመራቸው የቢሮክራሲ ውጣ ውረዶች በከፍተኛ ደረጃ እንዲቀንሱ ተደርጓል ብሏል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ የመንግሥት ክፍያዎችን በዲጂታል የክፍያ ሥርዓቶች እንዲፈጸሙ መደረጉ የምዝበራና የሙስና ቀዳዳዎችን በመዝጋት፣ የመንግሥትን ገቢ በከፍተኛ መጠን ለማሳደግ እና ሀብትን ለልማት ስራዎች ለማዋል አስቻይ ዐውድ መፍጠር አስችሏል። ለዚህ የዲጂታል ሽግግር የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ዋነኛ ምሰሶ ሲሆን፤ ዘርፉ በተለይም ለወጣቱ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ አስረድቷል። በቴክኖሎጂ ፈጠራ ላይ ለተሰማሩ ወጣቶች (ስታርትአፖች) ምቹ ምህዳር ከመፍጠር አኳያ የሕግ ማዕቀፎች መሻሻላቸው እና የፋይናንስ አቅርቦት አማራጮች መስፋፋታቸው ኢትዮጵያ በቀጣይ ዓመታት የአፍሪካ የቴክኖሎጂ ማዕከል እንድትሆን ጠንካራ መሰረት ጥሏልም ነው ያለው አገልግሎቱ በመግለጫው። መንግሥት ለዘርፉ የሰጠው ልዩ ትኩረት ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎችን ትኩረት ስቦ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ረገድ አበረታች ውጤቶች እያስመዘገበ መቀጠሉንም አመልክቷል።
ኢንተርፕራይዞቹ በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው
May 2, 2026 136
ሆሳዕና፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- በመንግሥት የተደረገላቸው ድጋፍ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር እንዳስቻላቸው በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተለያየ የሥራ መስክ የተደራጁ ኢንተርፕራይዞች ገለፁ፡፡   በጉራጌ ዞን አረቅጥ ከተማ የወሄነት ዳቦ ማምረቻና መሸጫ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ወጣት መሰረት ወልዴ እንዳለችው፤ ኢንተርፕራይዛቸው ከአባላቱ አልፎ ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር ችሏል። ከሦስት ዓመት በፊት በመንግሥት በተመቻቸላችው የ50 ሺህ ብር ብድር የማምረቻና የመሸጫ ሼድን ጨምሮ በተሰጣቸው የሥልጠና ድጋፍ ወደ ሥራ መግባታቸውን አውስታለች። ማኅበሩ አሁን ላይ የአባላቱን ተጠቃሚነት ከማሳደግ አልፎ፤ ለ 25 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን እና ከ11 ሚሊየን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገቡን ለኢዜአ አረጋግጣለች።   በቡታጅራ ከተማ የሚገኘው የአድማሱ ቶርኖ ሥራዎች አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ሥራ አስኪያጅ ወጣት ዳዊት አድማሱ፤ ኢንተርፕራይዙ የአርሶ አደሩን ምርት አሰባሰብ ሂደት የሚያዘምኑ ማሽኖችን መሥራቱን ገልጿል። ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ከመጠቀማቸው አልፎ፤ ለ13 ወጣቶችም የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ተናግሯል። ኢንተርፕራይዙ በ300 ሺህ ብር ሠራ መጀመሩን አውስቶ፤ አሁን ላይ ካፒታሉ 5 ሚሊየን ብር ደርሷል ብሏል።   የውኃ መሳቢያ ፓምፕ እና ሌሎች የፈጠራ ሥራዎችን ለገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን የገለጸው ደግሞ በሆሳዕና ከተማ የሚገኘው የአሚቼ ብረታ ብረትና እንጨት ሥራዎች ቴክኖሎጂ ሽግግር አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ተካልኝ ዓለሙ ነው። በተሰማሩበት ዘርፍ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ከመምጣቱ በተጨማሪ በቴክኖሎጂ ሽግግር ረገድ ሌሎች ወጣቶችን እያሰለጠኑ መሆኑንም አስታውቋል። በክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሙስጠፋ ኢሳ እንዳሉት፤ በአነስተኛ እና በመካከለኛ ደረጃ ለሚገኙ 3 ሺህ 620 አምራች ኢንተርፕራይዞች ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ነው። ኢንተርፕራይዞቹ ዘላቂና አስተማማኝ የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ለሀገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት የሚያበረክቱት አስተዋጽዖ ከፍተኛ መሆኑንም አመላክተዋል።
በከተማዋ ‎የተገነባው የመንግስት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር ሕንፃ ምቹ የሥራ ሁኔታ ለመፍጠርና ገቢን ለማጠናከር ያስችላል
May 2, 2026 69
ባህር ዳር፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ በባህር ዳር ከተማ ‎የተገነባው የመንግስት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር ሕንፃ ምቹ የሥራ ሁኔታን ለመፍጠርና ተጨማሪ ገቢን ለማጠናከር እንደሚያስችል የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ። በመንግስት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር በባህር ዳር ከተማ የተገነባው ባለ 9 ወለል ዘመናዊ መንትያ ሕንፃ ወደ ሥራ ገብቷል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በምረቃው እንደገለጹት ከጣና ሐይቅ በቅርብ ርቀት ላይ የተገነባው ሕንጻ በአካባቢው ከለማው የአረንጓዴ መዝናኛ ስፍራ ጋር ተዳምሮ የከተማዋን ገጽታ የቀየረ ነው። መንትያ ሕንፃው ከቢሮ አገልግሎት በተጨማሪ ለመዝናኛ፣ ለንግድ እንቅስቃሴ፣ ለስብሰባና ለቱሪዝም አገልግሎት የሚውል መሆኑን አመልክተዋል። ይህም ለተቋሙ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ በመሆን ኢኮኖሚያዊ አቅምን ከማጠናከር ባለፈ ምቹ የሥራ ሁኔታን እንደሚፈጥር ጠቁመዋል። በመንግስት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር የሰሜን ምዕራብ ሪጅን ጽህፈት ቤት ኃላፊ አስቻለው ሞላ በበኩላቸው መንትያ ሕንጻው ከ2 ቢሊየን ብር በላይ ወጭ የተገነባ መሆኑን ገልጸዋል። በጠቅላላ 2ሺህ 640 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ ያረፈው ሕንጻ ከቤዝመንት በተጨማሪ ዘጠኝ ወለል እንዳለውና ግንባታውም በተያዘለት ጊዜ እንደተጠናቀቀ ተናግረዋል። ሕንጻው ለተለያዩ አግልግሎቶች የሚውል በርካታ ክፍሎች ያሉትና ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች የተሟሉለት መሆኑንም አመልክተዋል። የሕንጻው ግንባታ ተቋሙ ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት እንዲሰጥ ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር መሆኑንም አክለዋል።
ሚኒስቴሩ የንግድ ስርዓቱን ከማዘመን ባለፈ በማህበራዊ ኃላፊነት ዘርፍ በርካታ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ ነው
May 2, 2026 75
ሮቤ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ የንግድ ስርዓቱን ከማዘመን ባለፈ ማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት በርካታ የልማት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ገለጸ። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከተጠሪ ተቋማቱ ጋር በመቀናጀት በባሌ ሮቤ ከ37 ሚሊዮን ብር በላይ ያስገነባቸው መኖሪያ ቤቶችን ለአቅመ ደካሞች አስረክቧል። የተገነቡት 20 መኖሪያ ቤቶች እያንዳንዳቸው የራሳቸው መሰረተ ልማትና የመኖሪያ ቁሶቁሶችን የተሟላላቸው መሆኑም ነው የተገለፀው። በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ የተገኙት የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ተቋሙ የንግድ ስርዓቱን ከማዘመን ባለፈ የማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት በርካታ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። ከዚህ ውስጥም በሀገሪቱ የተለያዩ ክልሎች ተመሳሳይ ዜጋ ተኮር ልማቶችና አገልግሎቶችን በማካሔድ ማሕበረሰቡን ተጠቃሚ በማድረግ ላይ እንደሚገኝ ነው የገለጹት። ዛሬ በባሌ ሮቤ ተገንብተው ለአገልግሎት የበቁት እነዚሁ ፕሮጀክቶች የዚሁ ጥረት ማሳያ መሆናቸውን አመልክተዋል። ፕሮጀክቶቹ በተለይ የአቅመ ደካማ ወገኖች የመኖሪያ ቤት ችግርን የሚቀርፉ ከመሆናቸው ባሻገር ፤ በዘርፉ የተያዙ ሀገራዊ ግቦችን ከማሳካት መንፃር ጉልህ ድርሻ ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የሚያካሒደውን የበጎ አድራጎት እንቅስቃሴ ይበልጥ የሚያጠናክሩና ቀጣይነት ያላቸው መሆናቸውንም አንስተዋል። ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት በራሳቸውና ሌሎች አካላትን በማስተባበር የገነቡትን ዲጂታል መፀሐፍት ቤት ለቀድሞ ትምህርት ቤታቸው የሮቤ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት አስረክበዋል። የመጽሃፍት ቤት ግንባታው የከተማዋን ወጣቶችና ተማሪዎች የንባብ ባህል ይበልጥ የሚያሳድግ ሲሆን የልጅነት ሕልማቸውንም ለማሳካት ያስቻላቸው መሆኑንም ገልፀዋል። የሮቤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ዲኖ አሚን በበኩላቸው ፤ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ለከተማዋ እድገትና ለአቅመ ደካማ ዜጎች ላደረገው ድጋፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። ከተማዋን ለነዋሪው ምቹና የንግድ ማእከል ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ውስጥ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እገዛ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ነው የገለጹት። ከልማቱ ተጠቃሚዎች መካከል ሼህ አልይ ከድርና ወይዘሮ ፋጡማ አብዳላ በበኩላቸው፣ የመኖሪያ ቤት ግንባታው ለዓመታት የነበረባቸውን የመጠለያ ችግር የሚቀርፍ መሆኑን ተናግረዋል።  
ሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትና ለኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ የሚያበረክት ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 2, 2026 207
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ለውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትና ለኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋፅኦ የሚያበረክት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በርትተን ከሰራን፣ ጀምረን ከጨረስንና ክፍተቶችን እያየን መሙላት ከቻልን፣ ዘላቂና ተከታታይነት ያለው ዕድገት በማስመዝገብ የኢትዮጵያን ብልፅግና በአጭር ጊዜ ውስጥ እውን እናደርጋለን ብለዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ በሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ውስጥ የሚገኘውን "ጎበዝ ሶላር ሴል" ማምረቻንና ሌሎች ፋብሪካዎችን ጎብኝተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በግል ባለሀብት የተገነባው ሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ከጅማና ከኮምቦልቻ ኢንዱስትሪ ፓርኮች በሦስት እጥፍ የሚበልጥ ሲሆን፣ ከሀዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክ ጋር ደግሞ በመጠን የሚስተካከል ነው። የሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ሠላሳ ሼዶች ያሉት መሆኑን ጠቅሰው፤ ስፋት ያለው፣ በርካታ ሰዎችን የሚይዝና ለከተማ በቅርብ ርቀት ላይ የሚገኝ በመሆኑ፣ የግል ዘርፉ በኢንቨስትመንት መስክ ያለውን ሚና አጎልቶ የሚያሳይ ነው ብለዋል። በጨርቃጨርቅ ላይ ተመስርቶ የነበረው የኢንዱስትሪ ፓርኮች ምርት አሁን ላይ እንዲሰፋ በተከናወነው ተግባር፤ ሶላር፣ የኤሌክትሪክ ባጃጅ፣ ጫማና አልባሳትን የመሳሰሉ ምርቶች በኢኮኖሚ ዞኑ እንደሚመረቱ ተናግረዋል። በኢኮኖሚ ዞኑ ባሉ ሼዶች የተለያዩ ምርቶች መመረታቸው የገበያ ዕድልን የሚያሰፋ መሆኑንም አንስተዋል። በኢኮኖሚ ዞኑ ያለው "ጎበዝ ሶላር ሴል" ማምረቻ አሁን ላይ ሁለት ጊጋ ዋት እያመረተ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይ ዓመት ተጨማሪ ሁለት ጊጋ ዋት ማምረት ይጀምራል ብለዋል። የሶላር ሴል ምርት በአጭር ጊዜ ውስጥ መመረት የጀመረና አሁን ላይ እየሰፋ ያለ መሆኑንም ተናግረዋል። ሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን በአዲስ አበባ የሚገኝና በርካታ ሼዶች ያሉት በመሆኑ፣ በርካታ የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ዕድል ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ኢንዱስትሪ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለኢነርጂና ለአገልግሎት ዘርፍ ዕድገት የሚውል በመሆኑ፣ በበርካታ መንገዶች በኢኮኖሚው ላይ አስተዋፅኦ የሚያበረክት እንደሆነም ገልፀዋል። ለውጭ ምንዛሬ ግኝት፣ ለእውቀት ሽግግርና ለሌሎች ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች የሚውል በመሆኑ፣ ጥቅሙን አሟጦ ለመጠቀም የተሳካውንና የሚቀረውን በመለየት በትኩረት መሥራት እንደሚጠይቅ አንስተዋል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ተግባራዊ ለውጥ እያስመዘገበና የኢንዱስትሪ ሽግሽግን እያመጣ ያለ መሆኑን ገልፀዋል። ይህን ማጠናከር ከተቻለ በቀጣዮቹ ዓመታት ኢትዮጵያ በብዙ መልኩ ራሷን የመቻል ዕድል እንዳላት የሚያመላክት መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የመጣውን ውጤት በማስፋትና በማሳደግ የኢትዮጵያን ብልፅግና ማረጋገጥ ከሁሉም የሚጠበቅ ዐቢይ ተግባር መሆኑን ገልፀዋል።
ለግብርና ኢንቨስትመንት በተፈጠረው ምቹ ሁኔታ የዘርፉ ውጤታማነት እያደገ ነው
May 2, 2026 127
ቦንጋ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ ለግብርና ኢንቨስትመንት የተፈጠረ ምቹ ሁኔታ የዘርፉን ውጤታማነት እንዳሳደገው ግብርና ሚኒስቴር ገለፀ። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር በግብርና ኢንቨስትመንት ከተሰማሩ ባለሀብቶችና ባለድርሻ አካላት ጋር ዛሬ በቦንጋ ከተማ መክሯል። በግብርና ሚኒስቴር የግብርና ኢንቨስትመንትና ምርት ግብይት መሪ ሥራ አስፈፃሚ ደረጀ አበበ እንደገለጹት መንግስት የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመንና የግል ባለሀብቱን ለማበረታታት የግብርናና ገጠር ልማት ፖሊሲ ቀርፆ ተግባራዊ አድርጓል።   ለዚህም ከግብዓት አቅርቦት ጀምሮ የተለያዩ የህግ ማዕቀፎችን በማሻሻል ለግል ባለሀብቱ በርካታ ማበረታቻዎችን በማድረግ ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል። የግብርና ኢንቨስትመንት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለውጭ ምንዛሬ ግኝትና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ የተለያዩ ምርቶችን ለማምረት አስተዋጽኦው የጎላ መሆኑንም አንስተዋል። ባለሀብቶች በገቡት ውልና በፖሊሲው በተቀመጠው መሰረት የወሰዱትን መሬት በአግባቡ ማልማት፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ በሰፊው መስራት እና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በትኩረት እንዲሰሩም አሳስበዋል። የመድረኩ ዓላማም በዘርፉ የተሰማሩ ባለሀብቶችን ችግር ለይቶ መፍትሄ ማበጀት፣ ትልልቅ የምግብ ዘይት አምራቾች በእርሻ ዘርፍ እንዲሳተፉ ማድረግና በሌሎች ጉዳዮች ላይ በመምከር ዘርፉን ይበልጥ ማጠናከር መሆኑንም ገልጸዋል።   ግብርና ለሀገር ኢኮኖሚ ያለዉ ድርሻ ከፍተኛ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ሀላፊ አስራት አስፋ ናቸው። ባለፉት ጊዜያት በዘርፉ በተሰሩ ስራዎች የተመዘገቡ ውጤቶችን ለማጠናከር ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡ በተለይም ባለሀብቶች በግብርና ኢንቨስትመንት ላይ እንዲሰማሩ ከፋይናንስ አቅርቦት ጀምሮ በርካታ ድጋፎች በተሻለ መልኩ እየተደረጉ ነው ብለዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት ለኢንቨስትመንት ዘርፍ በተሰጠ ትኩረት 544 ባለሀብቶች በግብርናው ዘርፍ መሰማራታቸውንና የዘርፉ ፍሰት በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መሆኑን ገልጸዋል። በዘርፉ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች 177ሺህ ሄክታር መሬት መመቻቸቱንና የህግና የአሰራር ማእቀፎች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።   በክልሉ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ በተሰራው ስራ የተሻለ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ያነሱት ደግሞ የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትልና የኢንቨስትመንት ዘርፍ ሀላፊ ከበደ ተስፋዬ ናቸው። ባለሀብቶቹ በቡና፣ በሰብል፣ በሻይ ልማት እንዲሁም በቅባት እህሎችና በሌሎች የግብርና ልማት ስራዎች መሰማራታቸውን አንስተው፣ ከእነዚህም ውስጥ 93ቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ወደ ስራ የገቡ አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች ናቸው ብለዋል።
ኢትዮጵያ የአፍሪካ የታዳሽ ኃይል ማዕከል የመሆን ጉዞዋን አጠናክራ ቀጥላለች
May 2, 2026 146
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአህጉሪቱ የታዳሽ ኃይል ልማት ማዕከልነቷን ለማረጋገጥ በጀመረችው ጉዞ ያስመዘገበቻቸውን ተጨባጭ ውጤቶች አጠናክራ መቀጠሏን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ገለጸ።   ኢትዮጵያ በታዳሽ የኃይል ምንጮች ላይ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም፣ የአፍሪካ ህብረትን የ2063 አጀንዳ ለማሳካትና አህጉሪቱን በኤሌክትሪክ ኃይል ለማስተሳሰር ቁልፍ ሚና እየተጫወተች ትገኛለች። አሁን ላይ ተግባራዊ እየሆኑ ያሉት የቀጣናው የኃይል ሽያጭ ስምምነቶችም፣ ሀገሪቱ የጀመረችው የብልፅግና ጉዞ በተጨባጭ ውጤት የታጀበ መሆኑን የሚያረጋግጡ ናቸው። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ የአይሻ 2 እና የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫዎች በስኬት ተጠናቅቀው ወደ ሥራ በመግባታቸው የሀገሪቱ የኃይል ማምረት አቅም ከ9 ሺህ 752 ሜጋ ዋት በላይ ደርሷል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መረጃ እንደሚያሳየው በ2018 በጀት ዓመት ዘጠኝ ወራት 24 ሺህ 970 ጊጋ ዋት ሰዓት ኃይል ለሀገር ውስጥና ለጎረቤት ሀገራት ለሽያጭ ቀርቧል። በበጀት ዓመቱ ለውጭ ሀገራት እና ለቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ከቀረበ የኃይል ሽያጭ 366 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ተገኝቷል። ይህም ካለፈው በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ138 ሚሊየን የአሜሪካን ዶላር ብልጫ እንዳለው ነው የተመለከተው።   የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል የኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ሞገስ መኮንን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ አሁን ላይ የኤሌትሪክ ኃይል የምታመነጨው ከውኃ፣ ከንፋስ ኃይል፣ ከፀሐይ ሐይል እና ከጂኦተርማል ነው። የኃይል አማራጭን ይበልጥ በማስፋት በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኃይል አቅርቦት ለመገንባት እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ የአፍሪካ የታዳሽ ኃይል ማዕከል ለመሆን የያዘችው ርዕይ በተጨባጭ ከጎረቤት ሀገራት ጋር በተፈጠረው የኢነርጂ መሠረተ ልማት ትስስር እየታየ መሆኑን ገልጸዋል። ከሱዳን፣ ከጅቡቲ፣ ከኬንያና ከታንዛኒያ ጋር የኃይል ሽያጭ ግንኙነት መጀመሩን ጠቅሰው፤ ይህም የሀገሪቱን በጋራ መልማት የሚለውን የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ እውን ከማድረግ ባለፈ በመተማመን ላይ የተመሰረተ ግንኙነት እንዲኖር ያደርጋል ብለዋል።   ይህ እንቅስቃሴ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት የአጀንዳ 2063 የመሰረተ ልማት ትስስር ግቦችን ለማሳካት ያላትን ግንባር ቀደም መሪነትና አስተዋጽኦ የሚያሳይ ነው ብለዋል። ከኃይል ሽያጭ የሚገኘው የውጭ ምንዛሬ ገቢ ለኃይል መሰረተ ልማቶች መስፋፋትና ጥገና ከፍተኛ እገዛ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። ለአብነትም የአይሻ ሁለት የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ግንባታ ወጪ በሀገር ውስጥ የፋይናንስ አቅም መሸፈኑን ጠቅሰው፤ ይህም የኃይል ተደራሽነትን ለማሳደግና ከብክለት ነጻ የሆነ ኢኮኖሚ ለመገንባት ለሚደረገው ጥረት ትልቅ አቅም ሆኗል ብለዋል።   ኢትዮጵያ የኃይል ሽያጭ ግቧን ከጎረቤት ሀገራት ባለፈ እስከ ደቡባዊ አፍሪካ ሀገራት ድረስ የማድረስ ሰፊ ዕቅድ ይዛ እየሰራች መሆኑንም ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅት ደቡብ ሱዳን የኃይል ፍላጎት በማሳየቷ የመግባቢያ ስምምነት ተፈርሞ በባለሙያዎች ደረጃ ዝርዝር ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። በተመሳሳይ ሶማሊያ የኃይል ፍላጎት እንዳላት የገለጹት ዳይሬክተሩ፤ የሌሎች ሀገራትን የኃይል መስመር በመጠቀም ድንበር ለማይጋሩ ሀገራት ጭምር ኃይል ለማቅረብ ዕቅድ መኖሩን አረጋግጠዋል።
የሌማት ትሩፋት ንቅናቄ ምርታማነትን በእጥፍ ማሳደግ አስችሏል
May 2, 2026 158
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ በመላው ሀገሪቱ በስፋት እየተከናወነ የሚገኘው የሌማት ትሩፋት ንቅናቄ ምርታማነትን በእጥፍ ማሳደግ ማስቻሉን ግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር በኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የተመጣጠነ ምግብ እጥረትን ለመቅረፍ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት ይፋ የተደረገ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው። ይህ የልማት ዕቅድ በዋናነት የወተት፣ የዶሮ፣ የማር፣ የሥጋ እና የዓሣ ሀብት ልማትን በቤተሰብ ደረጃ በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ያለመ ነው። በገጠርና በከተሞች በስፋት እየተተገበረ የሚገኘው ንቅናቄው የዜጎችን የምግብ አጠቃቀም ባህል በመቀየርና ራስን በምግብ ለመቻል የሚደረገውን ጥረት በማፋጠን ረገድ እንደ ዋና የልማት ምሰሶ ተደርጎ ይወሰዳል። ኢትዮጵያ ያሏትን ጸጋዎች በአግባቡ መጠቀም ከቻለችና ካለማች፣ የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶች የቅንጦት ምግቦች ሳይሆኑ ከሌማት መጥፋት የሌለባቸው እንደሆነ ታምኖበት በስፋት እየተሰራ ነው።   በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳት እና ዓሳ ሀብት ዘርፍ መሪ ስራ አስፈፃሚ አዚዝ አያሌው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሌማት ትሩፋት እየተከናወኑ የሚገኙት ተግባራት በምግብ ራስን ለመቻል የሚያግዙ ናቸው። የሌማት ትሩፋት ተግባራቱ ውጤት እያስመዘገቡ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ይህም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ አስቻይ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ባለፉት አራት ዓመታት በወተት፣ በዶሮ፣ በማርና ዓሳ ሀብት ዘርፍ ምርቶችን በእጥፍ ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል። በዚህም ለዜጎች ሰፊ የስራ እድል መፈጠሩንና የህብረተሰቡ ገቢ እንዲጨምር ብሎም የሀገር ኢኮኖሚ እንዲያድግ ማስቻሉን ተናግረዋል። በእንቁላል፣ በወተትና በስጋ ምርት ኢትዮጵያ ቀድማ የጀመረችው እንቅስቃሴ አሁን ያለውን የዓለም የገበያ ቀውስ ለማረጋጋት ትልቅ አቅም መፍጠሩንም ጠቅሰዋል፡፡ የሌማት ትሩፋት ምርታማነት ቀጣይነት እንዲኖረው የባለሀብቱ ተሳትፎ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመው፤ ባለሀብቱ በዘርፉ እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል። በዘርፉ የተሰማሩ አምራቾች በበኩላቸው፤ በሌማት ትሩፋት በመሰማራት ቤተሰቦቻቸውን ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ የተሻለ ገቢ እንዲኖራቸው እንዳስቻላቸው ይናገራሉ። አስተያየታቸውን ከሰጡ መካከል የተካልኝ ከበደ እና ጓደኞቻቸው ማህበር ዋና ስራ አስኪያጅ ተካልኝ አየለ፤ በሌማት ትሩፋት ዘርፍ በመሰማራት ተጨባጭ ውጤት ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡ በሥራው በርካታ ዓመታትን ማስቆጠራቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም ከእንስሳቱ በሚያገኟቸው ምርቶች ከራሳቸው ባለፈ የአካባቢውን ነዋሪዎች ተጠቃሚ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። በመሆኑም ወጣቶች በዘርፉ በመሰማራት የተሻለ ገቢ እንዲኖራቸውና ተሳታፊ እንዲሆኑም ጥሪ አቅርበዋል። አቶ ዘመኑ ታረቀኝ እና ወይዘሮ ጸዳለ እሸቴ፤ በሌማት ትሩፋት የሚያገኙት ውጤት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመምጣቱ፣ ከራሳቸው የዕለት ገበታ ባለፈ ለሌሎች በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደጋቸውን ተናግረዋል።
የሌማት ትሩፋት ዘላቂ ተጠቃሚነታችን እንድናረጋግጥ አግዞናል - የመርሐ-ግብሩ ተሳታፊዎች
May 2, 2026 92
ገንዳውኃ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር መሳተፋቸው ዘላቂ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ እንዳስቻላቸው በምዕራብ ጎንደር ዞን የሚገኙ ዜጎች ተናገሩ። የመተማ ዮሐንስ ከተማ ነዋሪ የሆነው ወጣት ሙሉ መርሻ ለኢዜአ እንደገለጸው፤ ከ2 ዓመት በፊት በ400 ሺህ ብር የጀመረውን የወተት ልማት ካፒታል አሁን ወደ 1 ነጥብ 6 ሚሊየን ብር አሳድጓል። ከ16 ላሞች የሚያገኘውን የወተት ምርትም ለገበያ በማቅረብ ዘላቂ ተጠቃሚነቱን እያረጋገጠ እንደሚገኝ ተናግሯል። በሌማት ትሩፋት መርሐ-ግብር በመታቀፍ በአምስት በሬዎች የጀመረውን የማድለብ ሥራ ይህን አሃዝ ወደ 15 ማሳደጉን የገለጸው ደግሞ የገንዳ ውኃ ከተማ ነዋሪ ወጣት ቢትወደድ አዳነ ነው። በዚህም ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ማረጋገጡን ጠቁሞ፤ ለውጤታማነቱም የባለሙያዎች ድጋፍና ክትትል ትልቅ ድርሻ እንዳለው አስታውቋል። በዶሮ ዕርባታ ሥራ በመሰማራት ከእንቁላል ሽያጭ ብቻ በወር እስከ 25 ሺህ ብር እንደሚያገኙ የገለጹት ደግሞ በከተማዋ በዘርፉ የተሰማሩት አስቴር ገበየሁ ናቸው። በወተት ልማት ዘርፍ ለመሰማርት ዝግጅት እያደረጉ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።   የምዕራብ ጎንደር ዞን እንስሳትና ዓሣ ሀብት ልማት መምሪያ ኃላፊ እያያው ታከለ እንዳሉት፤ ወጣቶችን በዘርፉ በማደራጀትና በግል ወደ ሥራ እንዲገቡ በስፋት እየተሠራ ነው። ባለፉት ዘጠኝ ወራትም ከ3 ሺህ 900 በላይ የኅብረተሰብ ክፍሎች 203 ሺህ የሚጠጉ በሬዎችን አድልበው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን የሚገኘውን የ“ጎበዝ ሶላር ሴል” ማምረቻን ጎበኙ
May 2, 2026 175
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፦‎ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ በሁዋጂያን ልዩ የኢኮኖሚ ዞን ውስጥ የሚገኘውን የ“ጎበዝ ሶላር ሴል” ማምረቻን ዛሬ ጎብኝተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ፋብሪካው በ2025 የኢንቨስትመንት ፎረም (Invest in Ethiopia Forum) አማካኝነት በተፈረመው ስምምነት መነሻ በ100 ሚሊየን ዶላር የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ የተቋቋመ መሆኑን አውስተዋል። በውጤታማ ድጋፍ እና ክትትል በስድስት ወራት ብቻ እውን የሆነው "ጎበዝ ሶላር ሴል" ማምረቻ ዘመናዊ ማሽኖች እና በቴክኖሎጂ የተዋቀረ ነው ብለዋል። ማምረቻው ለበርካታ ዜጎች የስራ እድልም መፍጠር መቻሉንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ አመልክተዋል።   በመጀመሪያ ምዕራፍ 2 ጌጋዋት ዓመታዊ የማምረት አቅም ያለው ፋብሪካው፣ የኢትዮጵያን የኃይል ፍላጎት ሙሉ በሙሉ ከታዳሽ ኃይል ለማድረግ የተጀመረውን ሀገራዊ ርዕይ እውን ለማድረግ ተደማሪ አቅም መፍጠሩን ነው ያብራሩት።   በዚሁ የኢንደስትሪ ፓርክ ውስጥ የሚገኘውን የጫማ ማምረቻ እና ንዑስ የኤሌክትሪክ ጣቢያን መመልከታቸውንም በመልዕክታቸው ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ENA
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም