ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የማስገንዘብ ስራዎች እየተሰሩ ነው
Nov 15, 2025 15
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሚያስገነዝቡ የዲፕሎማሲ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን በተለያዩ ሀገራት የሚገኙ የኢትዮጵያ ኤምባሲዎች ገለጹ። በዚምባብዌ የኢትዮጵያ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደርና በሞሪሽየስ፣ በዛምቢያ፣ በምስራቅና ደቡብ አፍሪካ አገራት የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) የኢትዮጵያ ተጠሪ ረሺድ መሀመድ፤ ኢትዮጵያ የባሕር በር ያጣችበት መንገድ በፖለቲካ አሻጥር የተሸረበ ኢ-ፍትሕዊ ውሳኔ እንደነበር አስታውሰዋል። ትልቅ የህዝብ ቁጥር ያላት ኢትዮጵያ የባሕር በር ተዘግቶባት ልትኖር እንደማትችል የቀረበው ፍትሕዊ ጥያቄም ዓለም አቀፍ ሕግ የሚደግፈው መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነትም የምስራቅ አፍሪካ ቀጣናን ሰላምና ደኅንነት በማስጠበቅ የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ ብሔራዊ ጥቅምን የማስጠበቅ አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያን ተፈጥራዊና ታሪካዊ ባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄም በዚምባብዌና ዛምቢያ ለሚገኙ የዲፕሎማቲክ ማህበረሰብ አባላት የማስገንዝብ ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ አንስተዋል። በኩዌት የኢትዮጵያ ኤምባሲ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ሰኢድ መሀመድ(ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄ ፍትሕዊ ተጠቃሚነትን የማስጠበቅ የህልውና ጉዳይ ነው ብለዋል። በዚህም የኢትዮጵያን የባሕር በር ጥያቄ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን በሁሉም አማራጭ ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ የማስገንዘብ ሚናቸውን እንዲወጡ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው በጋራ ተጠቃሚነት ዲፕሎማሲያዊ መርህ የቀረበ ጥያቄ መሆኑንም አስገንዝበዋል። በእንግሊዝ እና ሰሜን አየርላንድ የኢትዮጵያ አምባሳደር ብሩክ መኮንን ዳያስፖራው ኢትዮጵያ በሕዳሴ ግድብ ይደርስባት የነበረውን ጫና በመቋቋም ረገድ ቀዳሚ ሚና መወጣቱን አውስተዋል። ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የባህር በር ጥያቄን ተገቢነትና ፍትሃዊነት በማስረዳትም በኩል የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ እየተሰራ ነው ብለዋል። ኤምባሲው ዳያስፖራው በተለያዩ አማራጮች የኢትዮጵያን አቋም ተገቢነትና ፍትሃዊነት በማስረዳት እያደረገ ያለውን ድጋፍ ለማጠናከር እንደሚሰራም ተናግረዋል። የባህር በር ያጣነው ህጋዊ ባልሆነ መንገድና በተሳሳተ ፖሊሲ ነው ያሉት ደግሞ በደቡብ አፍሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲ በሚኒስትር ደረጃ የዳያስፖራ ዘርፍ ዲፕሎማት መላኩ ዘለቀ ናቸው። ዳያስፖራው ከዚህ ቀደምም የኢትዮጵያን እውነታ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የማሳወቅ ሚናውን ሲወጣ መቆየቱን ጠቅሰው፤ የባህር በር ጥያቄንም በማስረዳት በኩል ሚናውን እንደሚወጣ ተናግረዋል።
የሆሳዕና ከተማ የኮሪደር ልማት ለሌሎች ከተሞች ምሳሌ የሚሆን ነው
Nov 15, 2025 33
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ መፍጠርና መፍጠን በሚል እሳቤ የተሰራው የሆሳዕና ከተማ የኮሪደር ልማት ለሌሎች ከተሞች ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ ገለጹ። አቶ ተስፋሁን ጎበዛይ በሆሳዕና ከተማ የተሰሩ የኮሪደር ልማት ስራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከተመሰረተ አጭር ጊዜ ቢሆነውም በዋና ዋና ኢኒሼቲቮች የተሰሩና እየተሰሩ ያሉ የልማት ስራዎች በመደመር መንግሥት የተቀመጡ መፍጠርና መፍጠን የሚሉ እሳቤዎችን መሰረት ያደረጉ ናቸው ብለዋል።   በተለያዩ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተው በአጭር ጊዜ በሆሳዕና ከተማ የተሰራው የኮሪደር ልማት ለሌሎች ከተሞች ምሳሌ መሆን የሚችል ነው ሲሉ ገልጸዋል። ከተሞችን ውብና ጽዱ ለማድረግ በተጀመረው እሳቤ የሆሳዕና ከተማ የኮሪደር ልማት ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ በከፍተኛ ትጋት ከተሰራ ውጤት ማምጣት እንደሚቻል ማሳያ ነው ብለዋል። በክልሉ ያሉ እምቅ የተፈጥሮ ጸጋዎችን በአግባቡ በማስተዋወቅ ክልሉን የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ መገናኛ ብዙሃን የድርሻቸውን እንዲወጡም ጠይቀዋል።
ለብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን አከባበር በመሰረተ ልማት አስፈላጊው ዝግጅት እየተደረገ ነው - የሆሳዕና ከተማ አስተዳደር
Nov 14, 2025 69
ሆሳዕና፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሆሳዕና ከተማ ለሚከበረው የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በመሰረተ ልማት አስፈላጊው ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ። 20ኛው የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን "ዴሞክራሲያዊ መግባባት ለሀብረብሔራዊ አንድነት" በሚል መሪ ሀሳብ በፌዴሬሽን ምክር ቤት አስተባባሪነት በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሆሳዕና ከተማ ይከበራል። በዓሉ በፌደራል ደረጃ በሚከበርበት ሆሳዕና ከተማ ከማክበሪያ ስፍራና እንግዶች ማረፊያ ጀምሮ የተለያዩ ዝግጅቶች እየተደረጉ ነው። በዝግጅት ምዕራፍ ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች መካከል የመሰረተ ልማት ግንባታ ሥራዎች በዋናነት ይጠቀሳሉ።   የሆሳዕና ከተማ ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ዕህፈት ቤት ምክትል ሥራ አስኪያጅ ተከተል ጩፋሞ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በከተማው በፌዴራልና በከተማ አስተዳደሩ ከ30 ኪሎ ሜትር በላይ የአስፓልት መንገድ ሥራ እየተከናወነ ነው፡፡ በከተማ አስተዳደሩ በመጀመሪያ ምዕራፍ የ12 ነጥብ 4 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነና ልማቱ በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ከተማዋን ተወዳዳሪና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚገነቡ የመሰረተ ልማት ሥራዎች የብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦችን ቀን በዓልን ታሳቢ ባደረገ መልኩ እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። በተለይ የመንገድ መሰረተ ልማቱን ከበዓሉ አስቀድሞ ለማጠናቀቅ ትኩረት መሰጠቱን ነው ያመለከቱት።   በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የሶዶና አካባቢው ፕሮጀክቶች ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ሰለሞን ሞላ በበኩላቸው እንዳሉት ተቋሙ በራሱ ወጪ በከተማው የ10 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራ ያከናውናል። የመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ አካል የሆነው የ4 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትር የኮሪደር ልማት ሥራን በተያዘው ወር መጨረሻ በማጠናቀቅ ለበዓሉ ለማድረስ ርብርብ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የኮሪደር ልማቱ ሥራው የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገዶችን ጨምሮ የመዝናኛ፣ የአረንጓዴ ስፍራዎች፣ የመንገድ አካፋይና መብራቶችን ባካተተ መልኩ እየተከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡   የመሳይ ኦሊ ጠቅላላ ሥራ ተቋራጭ የሆሳዕና ከተማ ኮሪደር ልማት ፕሮጀክት ሥራ አስኪያጅ ታደሰ አማኑኤል በበኩላቸው፣ ልማቱን በታቀደው ጊዜ ለማጠናቀቅ ቀንና ማታ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ የኮሪደር ልማት ሥራውን ለኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓል ለማድረስ በርብርብ እየተሰራ መሆኑንም አመልክተዋል።   በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች ከተማዋን ለነዋሪው ምቹ ከማድረግ ባለፈ ከአቻ ከተሞች ጋር ተወዳዳሪ የሚያደርጋት ነው ያሉት ደግሞ የከተማው ነዋሪ እሸቱ ኃይሌ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በከተማው መከበር የህዝብ ለህዝብ ትስስርን ከማጠናከር ባለፈ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎች እንዳሉት ተናግረዋል፡፡
ቅርሶችን በመጠበቅ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸውን ለማጎልበት የተሰሩ ተግባራት አበረታች ውጤቶች እያስገኙ ነው
Nov 14, 2025 69
ድሬዳዋ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ ቅርሶችን በመጠበቅ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸውን ለማጎልበት የተሰሩ ተግባራት አበረታች ውጤቶች እያስገኙ መሆኑን የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ህይወት ኃይሉ ተናገሩ። የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን " በተቀናጀ ትብብር ህገ ወጥ የቅርስ ዝውውርን እንከላከል " በሚል መሪ ሃሳብ ህገ- ወጥ የቅርስ ዝውውር መከላከል ዓለምአቀፍ ቀንን ዛሬ በድሬዳዋ በውይይት አክብሯል ። የኢትዮጵያ ቅርስ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ህይወት ኃይሉ በወቅቱ እንዳሉት ቅርሶችን በመጠበቅ ለአገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት የሚያበረክቱትን ፋይዳ ለማጎልበት የተሰሩ ተግባራት አበረታች ውጤቶች እያስገኙ ነው። ቅርሶችን በዲጂታል ቴክኖሎጂ በመመዝብ፣ ደረጃ በማውጣትና በማልማት ሁለንተናዊ አብርክቷቸውን እውን ለማድረግ በትኩረት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በፌደራልም ሆነ በክልሎች የሚገኙ ቅርሶች ላይ ምርምሮችና ዕድሳትን በማካሄድ ቅርሶቹ ተጠብቀው ለትውልድ እንዲተላለፉም እየተሰራ መሆኑን አክለዋል። በተለይ ከለውጡ በኃላ ለቅርሶች ጥበቃና እድሳት ልዩ ትኩረት በመስጠት ለቱሪስት መዳረሻ እንዲያገለግሉ መደረጉን አንስተዋል። በጅማ አባጅፋር፣ በጎንደር፣ በሶፍ ኡመር ዋሻ እና በሌሎች ቅርሶች ላይ የተሰሩ ስራዎችንም በማሳያነት አቅርበዋል። ከእድሳትና ጥበቃ በሻገርም በተለያዩ ወቅቶች በህገ ወጥ መንገድ ከአገር የወጡ 44 ቅርሶችን ከቅርስ አስመላሽ ኮሚቴ ጋር በመቀናጀት ማስመለስ መቻሉን ተናግረዋል ። እነዚህን አበረታች ስራዎች ለማጠናከርና ህገ ወጥ የቅርስ ዝውውርን ለመከላከል ከአየር መንገድ፣ ከጉምሩክ፣ ከፍትህና ፀጥታ ፣ ከኃይማኖት አባቶች ጋር ዛሬ የተካሄደው ውይይት አጋዥ እንደሚሆን ጠቁመዋል። በውይይቱ ላይ የተሳተፉት የድሬዳዋ አስተዳደር የባህልና ቱሪዝም ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወንደሰን አባይ በበኩላቸው ከባለስልጣኑ ጋር በመቀናጀት ቅርሶችን የመጠበቅ፣ የማልማት፣ የማደስና የመመዝገብ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። በተለይ ባለስልጣኑ፣ የ16ተኛዉ ክፍለ ዘመን የስልጣኔ አምባ የነበረውን የሐርላ መካነ ቅርስ እና 130 አመታት ያስቆጠረው የባቡር ተርሚናል በተገቢው መንገድ በማደስ ለቱሪስት መዳረሻነት እንዲውሉ መደረጉ ከዘርፉ የተሻለ ጥቅም እንዲገኝ መደላድል መፈጠሩን ጠቅሰዋል። እነዚህን ሃብቶች በተገቢው መንገድ መጠበቅና መንከባከብ የሁሉም ዜጋ ኃላፊነት መሆኑን ገልጸዋል ። የተካሄደው የግንዛቤ ማጎልበቻ ውይይት በዘርፉ የተጀመሩ አበረታች ስራዎችን ተቀናጅቶ ለማሳደግ የሚያስችል መሆኑን አመልክተዋል።
የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የማዕድን ጸጋዎችን ለማልማት ወሳኝ አቅም ፈጥሯል
Nov 14, 2025 63
አዲስ አበባ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የማዕድን ጸጋዎችን ለማልማት ወሳኝ አቅም መፍጠሩን በ4ኛው ዓለም አቀፍ የማዕድንና ቴክኖሎጂ ኤክስፖ ተሳታፊ አልሚዎች ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ 4ኛውን ዓለም አቀፍ የማዕድንና ቴክኖሎጂ ኤክስፖ(MINTEX Ethiopia 2025) በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል መርቀው ከፍተዋል። ከኅዳር 4 እስከ 7/2018 ዓ.ም በሚቆየው ኤክስፖ ላይ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የሀገር ውስጥና የውጭ አልሚ ባለሃብቶችን፣ ቴክኖሎጂ አምራቾች፣ ምሁራን እና አጋሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። የኤክስፖው ተሳታፊ የሀገር ውስጥና የውጭ አልሚዎች ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ በማዕድን ዘርፍ የኢንቨስትመንት አቅምን ለማስፋት አበረታች የልማት ምኅዳር መፈጠሩን ገልጸዋል። የአኮቦ ሚኒራልስ ዋና ስራ አስፈጻሚ ጆርገን ኤቭጀን፤ የማዕድን ኤክስፖው ምርትና አገልግሎታቸውን በማስተዋወቅ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ጉልህ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ለማዕድን ዘርፍ የኢንቨስትመንት ከባቢ የፈጠረው የማበረታቻ ምኅዳር የወርቅ ማዕድን ልማት ስራን ለማስፋት አቅም እየፈጠረላቸው እንደሚገኝ ገልጸዋል። ሌላኛው የጂ.ሲ.ኤል ኢትዮጵያ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሊ ጂያንጁን በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ የተፈጠረው ምቹ የኢንቨስትመንት ምኅዳር ሀገሪቱን ተመራጭ የልማት መዳረሻ እያደረጋት ነው ብለዋል። ድርጅታቸው በኢትዮጵያ ከአሥር ዓመታት በላይ ያደረገው የነዳጅ ፍለጋ ፍሬ አፍርቶ የተፈጥሮ ጋዝ በማስመረቅ ሁለተኛውን ምዕራፍ ግንባታ እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የተፈጥሮ ማዕድን ሃብት ጸጋዎችና ምቹ ኢንቨስትመንት መዳረሻነትን በመጠቀም ግዙፉ የድፍድፍ ነዳጅ ማጣሪያ ግንባታ ላይ እንዲገቡ ማስቻሉን ተናግረዋል። በቀጣይም የነዳጅና የተፈጥሮ ጋዝ ምርት ልማት አቅምን በማሳደግ ኢትዮጵያን የኃይል አቅርቦት ማዕከል ለማድረግ በትጋት እንደሚሰሩ አስረድተዋል። የኢምራን ጂምስቶን ዋና ዳይሬክተር ቢኒያሚን አቡበከር፤ የኢትዮጵያ መንግስት ለሀገር ውስጥና ለውጭ ባለሃብቶች የሚሰጠው ድጋፍ በማዕድን ልማት ከፍተኛ መነቃቃት እየፈጠረ ነው ብለዋል። ለማዕድን አልሚዎች የተፈጠረው ምቹ የኢንቨስትመንት ምኅዳር ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የማዕድን ፍለጋ ልማት ስራን የሚያከናወኑበት ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል። በማዕድን ልማት ለተሰማሩ አልሚዎች የሚሰጠው የፋይናንስ አቅርቦት ከፍተኛ ዕድገት እያስመዘገበ ነው ያሉት ደግሞ በዳሸን ባንክ የማርኬቲንግ ክፍል የሽያጭ ኃላፊ ነጋ ሽባባው ናቸው። በቀጣይም የኢትዮጵያን የማዕድን ሃብት ልማት ለማጠናከር የከበሩ ማዕድናት ካዝናን ጨምሮ የውጭ ምንዛሬ የገንዘብ አቅርቦት የማመቻቸት ስራዎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።
የባሌ ዞን የቱሪስት መዳረሻዎች ልማት የቱሪስት ፍሰቱ እንዲጨምር አድርጓል
Nov 14, 2025 120
ሮቤ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በባሌ ዞን የቱሪስት መዳረሻዎችን ለማልማትና ለማስተዋወቅ የተሰሩ ተግባራት የቱሪስት ፍሰቱ እንዲጨምር ማድረጋቸውን የዞኑ ቱሪዝም ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ በቱሪስቶች አገልግሎት ሰጪ ተቋማት የተሰማሩ ነዋሪዎችና ማህበራትም ከዘርፉ ተጠቃሚነታቸው ማደጉን ገልጸዋል። በጽህፈት ቤቱ የቱሪዝም ልማትና ማስፋፊያ ቡድን መሪ ሽብሩ አብዶ ለኢዜአ እንደተናገሩት የዞኑን የቱሪስት መስህቦች በማልማትና በማስተዋወቅ የዘርፉን አኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ለማሳደግ እየተሰራ ነው።   ይህም ዞኑን የሚጎበኙ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገራት ቱሪስቶች ቁጥር እንዲጨምር በማድረጉ በበጀት አመቱ የመጀመሪያው ሩብ አመት 16ሺህ 217 ቱሪስቶች መዳረሻዎቹን ጎብኝተዋል ብለዋል፡፡ መስህቦቹን የጎበኙት ቱሪስቶች ቁጥር ካለፈው አመት ተመሳሳይ ወራት ጋር ሲነጻጸር በ15 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን አመልክተዋል። የቱሪስት መዳረሻ ልማቱ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ከማሳደግ ባለፈ የአካባቢውን ባህል ለማስተዋወቅና በዘርፉ ለተሰማሩ አካላት ተጨማሪ ገቢ እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አክለዋል።   ለአብነትም በሩብ አመቱ አካባቢውን ከጎበኙ ቱሪስቶች ከ25 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን በማሳያነት አንስተዋል። ለቱሪስቶች ቁጥር መጨመር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በአካባቢው እየተከናወኑ ያሉ መሰረተ ልማቶች እና አካባቢውን ለማስተዋወቅ የተደረጉ የተቀናጁ ጥረቶች እና የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ በዩኔስኮ በቋሚ ቅርስነት መመዝገብ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። በቱሪስት አገልግሎት ሰጪ ተቋማት መካከል በሮቤ ከተማ የቱሉ ሀምበላት የባህል ልብስ ቤት ተወካይ ወይዘሮ መርየማ ከድር ባሌ ሮቤን ለሚጎበኙ ለሀገር ውስጥና ለውጭ ቱሪስቶች የባህል አልባሳት እንደሚሸጡ ተናግረዋል። የቱሪስቶች ቁጥር መጨመርና በተለያዩ ዲዛይኖች የሚያዘጋጁት የባህል አልባሳት ጥራት በሥራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ ማገዙን አስረድተዋል። የባሌ ፓርክን በአስጎብኚነትና በመንገድ በመምራት አገልግሎት የተሰማራው የዋሊያ ኢኮ-ቱሪዝም ማህበር ስራ አስኪያጅ ጃፈር መሐመድ በበኩሉ ፓርኩን ለማልማት የተደረገውን ጥረት ተከትሎ የጎብኚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል። ይህም የማህበሩ አባላትም መንገድ በመምራት፣ ፈረስ በማከራየት የሚያገኙት ገቢ እንዲጨምር ማድረጉን ተናግረዋል። በባሌ ዞን በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባህል ድርጅት/ዩኔስኮ/ በአለም የተፈጥሮ ቅርስነት የተመዘገበውን የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን ጨምሮ ሌሎች ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ መስህቦች ይገኛሉ።
የስንዴ ምርትን ከብክነትን በፀዳ መልኩ የመሰብሰብ ተግባር በምስራቅ ጉራጌ ዞን
Nov 14, 2025 53
ወልቂጤ፤ ህዳር 5/2018 (ኢዜአ)፦ የደረሰ የስንዴ ሰብል ምርትን በኮምባይነር በመታገዝ ብክነትን በሚቀንስ መልኩ እየሰበሰቡ መሆኑን የምስራቅ ጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች ተናገሩ፡፡ መንግስት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በግብርናው መስክ ከጀመራቸው ተግባራት መካከል የስንዴ ልማት በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው፡፡ ይህም ከውጪ ይገባ የነበረውን የስንዴ ምርት በሀገር ውስጥ በመተካት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ወጪን አስቀርቷል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ስንዴን በሰፋፊ ማሳዎችና በቴክኖሎጂ በመታገዝ የማልማት ስራው የተጠናከረ ሲሆን በተለያዩ አካባቢዎችም በኩታ ገጠም አስተራረስ አርሶ አደሮችን በማደራጀት እየተከናወነ ነው፡፡ በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምስራቅ ጉራጌ ዞንም የስንዴ ልማት ስራው በትኩረት እየተከናወነ ሲሆን የደረሰውም ምርት በኮምባይነር በመታገዝ ፈጥኖ በመሰብሰብ የምርት ብክነትን ለመከላከል እየተሰራ ነው፡፡ ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የዞኑ አርሶ አደሮች እንደተናገሩትም የደረሰ የስንዴ ምርታቸውን በኮምባይነር በመታገዝ ከብክነት በጸዳ መልኩ እየሰበሰቡ ነው፡፡ በምስራቅ መስቃን ወረዳ የባቲሊጃኖ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር መለሰ ኡርጋቶ በመኸር ወቅት ከ4 ሄክታር በላይ መሬትን በስንዴ ሰብል ማልማታቸውን ገልጸዋል፡፡ በባለሙያዎች ክትትልና ድጋፍ በመታገዝ ያለሙትን የስንዴ ሰብል ከብክነት በጸዳ መልኩ በኮምባይነር መሰብሰባቸውን ተናግረዋል። በሶዶ ወረዳ የኤጀርሳ ቀበሌ አርሶ አደር ሃይሌ ሀብታሙ በበኩላቸው በመኸር ወቅት ሦስት ሄክታር የሚጠጋ ማሳን በስንዴ ሰብል ማልማታቸውን ጠቁመዋል፡፡ የደረሰውን የስንዴና የጤፍ ሰብላቸውን ወቅቱን ካልጠበቀ ዝናብ ለመከላከል ቀድመው እየሰበሰቡ እንደሚገኙ ገልጸው፤ ጊዜና ጉልበት የሚቆጥቡና ምርትን ያለ ብክነት ለመሰብሰብ የሚያስችሉ ዘመናዊ ማሽኖች በመንግስት እንደተመቻቸላቸውም ተናግረዋል፡፡ የምስራቅ ጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ደሱ አበጋዝ እንዳሉት በዞኑ ለምግብ ፍጆታና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚውል ስንዴ በስፋት እየተመረተ ነው፡፡ በዞኑ በመኸር ከተሸፈነው ከ20 ሺህ ሄክታር በላይ የስንዴ ማሳ 13 ሺህ 772 ሄክታሩ በኩታ ገጠም የለማ መሆኑን ጠቅሰው ከ1 ሚሊዮን 300 ሺህ በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ገልጸዋል፡፡ የደረሱ ሰብሎችን በፍጥነትና ከብክነት በጸዳ መልኩ በማሽን በመታገዝ የመሰብሰብ ተግባር እየተከናወነ ነው ብለዋል፡፡ ስንዴን ጨምሮ የደረሱ ሰብሎችን ፈጥነው በመሰብሰብ ወቅቱን ካልጠበቀ ዝናብና የምርት ብክነት የመከላከል ተግባር እየተከናወነ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የሶዶ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና ግብርና ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሸጋ ሃብቴ ናቸው። የምስራቅ መስቃን ወረዳ ግብርና ፅህፈት ቤት ምክትልና የእርሻ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ሁሴን ሙስጠፋ በበኩላቸው በወረዳው ምርትን ከብክነትን በፀዳ መልኩ በመሰብሰብ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ ነው ብለዋል።
በጅማ ከተማ ስምንት የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎችን በማቋቋም የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት እየተሰራ ነው
Nov 14, 2025 57
ጅማ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በጅማ ከተማ ስምንት የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎችን በማቋቋም የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት እየተሰራ መሆኑን የከተማው ንግድ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የከተማው ንግድ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ጉተማ ጊዲ ለኢዜአ እንዳሉት በከተማው የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የሚያግዙ የተለያዩ ስራዎች እየተከናወኑ ነው። በተለይም የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎችን በማስፋፋት የምርት አቅርቦትና ተደራሸነት እንዲጠናከር የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በከተማው ስምንት የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች ተደራጅተው ምርቶች፣ ሸቀጦችና ሌሎች የፍጆታ እቃዎች ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ ገበያዎቹ አምራች እና ሸማቹን ስለሚያገናኙ በህገ ወጥ ነጋዴዎች የሚፈጠረውን ሰው ሰራሽ የዋጋ ንረት ለመከላከል እያገዙ ነው ብለዋል። በተጨማሪም በሸማች ህብረት ስራ ማህበራት አማካኝነት ሸቀጦችና ምርቶች ለህብረተሰቡ እንዲቀርቡ እየተደረገ መሆኑንም አውስተዋል። ከዚህ ጎን ለጎንም በህገ ወጥ ንግድ ላይ የተሰማሩ ነጋዴዎችና የንግድ ተቋማት ላይ አስተዳደራዊና ህጋዊ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን አስረድተዋል።   በተለይም ያለበቂ ምክንያት ዋጋ በሚጨምሩና ምርት በሚደብቁ ነጋዴዎች ላይ አስተዳደራዊ እርምጃዎች እየተወሰደ እንደሆነ ጠቁመው እርምጃው ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በተሰራው ስራ በከተማዋ የተረጋጋ የግብይት ሁኔታ መኖሩን አመልክተው ከአምራቾችና ከጅምላ ነጋዴዎች ጋር በመቀናጀት የምርት አቅርቦት ስራው ይጠናከራል ነው ያሉት። በከተማው ከሚገኙ የሸማች ህብረት ስራ ማህበራት መካከል የጊንጆ ጉዱሩ ማህበር ሊቀመንበር ኦላኒ ቀልቤሳ፣ በማህበሩ የተለያዩ ምርቶችና ሸቀጦችን ለሸማቹ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረበ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም ጤፍ፣ ስንዴ፣ በቆሎና ሌሎች የግብርና ምርቶችን ጨምሮ ስኳርና ዘይት እያቀረቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ከከተማው ነዋሪዎች መካከል ኤሊያስ አባጀበል፣ በከተማዋ የተጀመረው ገበያን የማረጋጋት ስራ ውጤታማ በመሆኑ መጠናከር አለበት ብለዋል። አሁንም ያለበቂ ምክንያት ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉ ነጋዴዎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ መጠናከር እንዳለበትም ጠቁመዋል። በከተማው በተቋቋሙ የቅዳሜ እና እሁድ ገበያዎች የምርት አቅርቦቱ የተሻለ መሆኑን የገለጹት ደግሞ ሌላው የከተማው ነዋሪ አብዱል ባሲጥ አባ ገሮ ናቸው። በአንዳንድ ነጋዴዎች ላይ የተጀመረው ክትትልም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አመልክተዋል።
በመፍጠንና በመፍጠር ኢትዮጵያን መገንባት የሚያስችል የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም እየተተገበረ ነው
Nov 14, 2025 78
አዲስ አበባ፤ ህዳር 5/2018(ኢዜአ)፦ በመፍጠንና በመፍጠር ቴክኖሎጂን በመተግበር ኢትዮጵያን መገንባት የሚያስችል የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም እየተተገበረ መሆኑን የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ኃይሌ(ዶ/ር) ገለጹ። ይህ የተገለጸው የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ባዘጋጀው የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም የተሞክሮ ልውውጥ መድረክ ላይ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) "የመደመር መንግሥት ዕይታ ለዘርፎች እመርታ" በሚል መሪ ሐሳብ በተዘጋጀው ስልጠና ወቅት የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርሙ ሙሉ በሙሉ መጠናቀቅ እንዳለበት አቅጣጫ ማስቀመጣቸው ተገልጿል። የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽነር መኩሪያ ኃይሌ(ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የመንግሥት አገልግሎትና አስተዳደር ሪፎርም ሒደት ኢትዮጵያ ለተሞክሮ ወደ ውጭ መሄድ የለባትም በሚል መነሻ በሀገር ልጆች የተቀረጸ ነው። በዓለም ላይ የበለጸጉ ሀገራት ጭምር የተሳካ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርምን ለመተግበር እስከ 300 ዓመት ወስዶባቸዋል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በመደመር ዕሳቤ ሪፎርም እንዲደረግ ባስቀመጡት አቅጣጫ መሠረት የተከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል። ከዚህ አንፃር የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስቀመጡት አቅጣጫ መሠረት ሥራውን በብቃት እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል።   የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር በሪፎርሙ የመደመር ሥራ ምን እንደሚመስል በተግባር መሬት ላይ አሳይቶናል ብለዋል። የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርሙ ቁርጠኝነትና ውጤታማነት የታየበት ድንቅ ስኬት መሆኑን በማንሳት፤ ይህም ከሀገር አልፎ በአፍሪካም ለተሞክሮ መቅረብ እንደሚችል ገልጸዋል። በኢትዮጵያ በመፍጠርና በመፍጠን ቴክኖሎጂን ተግባራዊ በማድረግ ኢትዮጵያን መገንባት የሚያስችል ሪፎርም ተደርጓል ብለዋል። ሁሉም የተሳተፉበት በሀገር ልጆች የተሰራ ሪፎርም መሆኑን ጠቅሰው፤ ለሪፎርሙ 14 የትግበራ ስትራቴጂዎች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ጥሩ የሠሩ ሠራተኞች የሚበረታቱበት ሥርዓት አስፈላጊ መሆኑን ገልጸው፤ የሀሳብ ባንክ መዘጋጀቱ ከበለጸጉ ሀገራት ጭምር ቀድመን የሄድንበት ነው ብለዋል። ሪፎርሙ የሚሠሩ ሥራዎችን ለይቶ ማስቀመጡን ጠቅሰው፣ መተግበሪያ መሣሪያዎች በራሳቸው ነባራዊ ሁኔታ ተግባራዊ እንዲያደርጉ ዕድል መስጠቱን ገልጸዋል። የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርሙን ለማሳካት የጎላ አበርክቶ ያለው በመሆኑ ለሪፎርሙ ስኬታማነት የተሰጠውን ዕድል በአግባቡ መጠቀም እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በጉጂ ዞን በአትክልት ልማት የተሰማሩ ነዋሪዎች ተጠቃሚ እየሆኑ ነው
Nov 14, 2025 120
አዶላ ፤ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በአትክልት ልማት የተሰማሩ ነዋሪዎች ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ገለጹ። በዞኑ በአነስተኛ የመስኖ ልማት ተሰማርተው የምግብ ዋስትናቸውን እያረጋገጡ ካሉ የአዶላ ከተማ ነዋሪዎች መካከል ምህረት ይልማ፤ ባለፉት አራት አመታት ሰላጣ፣ ጎመን፣ ቆስጣ፣ ቃሪያና ፓፓያ ማልማታቸውን ገልጸዋል፡፡   የመስኖ ልማት ስራቸው ውጤታማ በመሆኑም ከጉጂ ዞንና ከአዶላ ከተማ አስተዳደር የእውቅና ሽልማት ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ ሽልማቱ በፈጠረላቸው መነሳሳት ጠንክረው በመስራት በአትክልትና ስራስር ልማቱ ገቢያቸውን ማሳደግ መቻላቸውን ገልጸዋል፡፡ የጀመሩት አነስተኛ የመስኖ ልማት የተመጣጠነ ምግብን ከማግኘት ባለፈ ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን ማሳደግ እንደቻሉ ጠቁመዋል፡፡ የአዶላ ወረዳ ነዋሪው አቶ ጀማል ጉራቻ በበኩላቸው፤ ፓፓያ፣ ድንች፣ ቲማቲምና ቀይ ሽንኩርት በማምረት ለገበያ አቅርበው ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡   የመስኖ ልማት በትንሽ መሬት ላይ ብዙ በማምረት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንዳገዛቸው ገልጸው ለሌሎች አርሶ አደሮች ልምዳቸውን ማካፈላቸውን ተናግረዋል፡፡ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ መንግስቱ ሂርባዬ እንዳሉት፤ በዞኑ በአነስተኛ መስኖ የአትክልት ልማት ስራ ከ25 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች እየተሳተፉ ነው፡፡   ልማቱም የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ከሚያበረክተው ፋይዳ ባለፈ ገበያን ለማረጋጋት የራሱን ድርሻ ማበርከቱን አክለዋል። የመስኖ ልማቱን ውጤታማ ለማድረግ የግብአት አቅርቦትና የግብርና ባለሞያዎች ክትትል እንዲሁም ለአርሶ አደሮች ግንዛቤ መሰጠቱን ገልጸዋል። በዚህም ድንች፣ ቀይ ሽንኩርት፣ ጥቅል ጎመን፣ ካሮት፣ ቀይስር፡፤ ቲማቲም፣ ቃሪያ፣ ሙዝና ፓፓያ በስፋት እየለማ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
በሰሜን ወሎ ዞን በሚገኙ ሶስት ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራ እየተከናወነ  ነው 
Nov 14, 2025 109
ወልዲያ ፤ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡-በሰሜን ወሎ ዞን ሶስት ከተሞች የኮሪደር ልማት እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ከተሞችና መሠረተ ልማት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ መኮንን የሱፍ ለኢዜአ እንደገለጹት የኮሪደር ልማት ስራው እየተከናወነባቸው የሚገኙት የቆቦ፣ የመርሳና የጋሸና ከተሞች ናቸው። በሶሰቱም ከተሞች የ11 ኪሎ ሜትር የአስፋልት፣ የእግረኛ፣ የሳይክልና ሌሎች መሰረተ ልማቶችን ያሟላ የኮሪደር ልማት እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል። በተጨማሪም የውሃ ማፋሰሻ ቦዮች፣ ድልድዮችን፣ ደረጃውን የጠበቀ የመንገድ መብራት፣ የመዝናኛ ስፍራዎች፣ የአረንጓዴ ልማትና ሌሎች መሰረተ ልማትን አካቶ እንደሚገነባ ተናግረዋል።   አሁን ላይ የግንባታ አካባቢዎችን የማጽዳት፣ የቁፋሮና አፈር ቆረጣ እንዲሁም የገረጋንቲ ሙሌት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው በዚህም ለበርካታ ወጣቶች የስራ እድል ተፈጥሯል ብለዋል። የኮሪደር ልማቱ እየተከናወነ የሚገኘውም ከከተሞቹ መስተዳድሮች፣ ከነዋሪዎችና ባለሃብቶች በሚሰበሰብ ከ950 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ መሆኑን ገልጸዋል። በሃምሌ ወር 2017 ዓ.ም የተጀመረው የኮሪደር ልማት አሁን ላይ አፈጻጸሙ 25 በመቶ መድረሱን ጠቁመው በያዝነው በጀት ዓመት መጨረሻ ለማጠናቀቅ ጥረት እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል።   የቆቦ ከተማ ነዋሪው አቶ ወንድምነው ሞላ በሰጡት አስተያየት ከተማችንን ለማስዋብና ደረጃዋን የጠበቀች ለማድረግ ከመስተዳድሩ ጋር በመተባበር የኮሪደር ልማቱን እያካሄድን እንገኛለን ብለዋል። መስተዳድሩ ከህብረተሰቡ ጋር ባካሄደው ውይይት የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ ስራው እየተከናወነ መሆኑን አረጋግጠዋል። የመርሳ ከተማ ህዝብ አሸዋና ድንጋይ በማቅረብ፣ ገንዘብ በማዋጣትና ሌሎች ድጋፎችን በማድረግ ለኮሪደር ልማቱ የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የከተማዋ ነዋሪ አቶ አህመድ የሱፍ ናቸው። በሌሎች ከተሞች የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ስራዎች በቁጭት እንድንነሳ አድርጎናል ሲሉም ተናግረዋል።
የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር አስችለዋል
Nov 14, 2025 74
አዲስ አበባ፤ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡-ባለፉት ዓመታት ህዝብን በማሳተፍ የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአፈር ለምነትን በማሳደግ ምርት እና ምርታማነት እንዲጨምር ማስቻሉን ግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። ለዘንድሮ በጋ ተፋሰስ አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ምዕራፍ እየተጠናቀቀ መሆኑም ተገልጿል። የአየር ንብረት ለውጥ፣ ጎርፍ፣ የዝናብ መዛባት፣ ድርቅና የአፈር መሸርሸር የስነ ምህዳር መጓደል በማስከተል የሰውን ልጅ ለከፋ ጉዳት ይዳርጋሉ፡፡ ችግኝ መትከል፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ማከናወን ደግሞ የተፈጥሮን ስነ ምህዳር በማስተካከል የሰውን ልጅ ከከፋ ጉዳት ለመጠበቅ ያስችላል፡፡   በኢትዮጵያ በመከናወን ላይ የሚገኙት የአረንጓዴ አሻር መርኃ ግብርና የበጋ የተፋስስ ልማት ስራዎች ሀገሪቱ ለአካባቢ ጥበቃ የሰጠችውን ከፍተኛ ትኩረት የሚያሳዩ ናቸው፡፡ በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈጻሚ አቶ ፋኖሴ መኮንን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ የተፈጥሮ ሃብት ከሰው ልጅ ኑሮ ጋር ከፍተኛ ቁርኝት አለው ብለዋል፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ፣ ጎርፍ፣ ድርቅና የአፈር መሸርሸር የሚከሰተው ሰዎች በተፈጥሮ ላይ ለሚያደርሱት ጉዳት በሚሰጥ የተፈጥሮ ምላሽ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡   ባለፉት ዓመታት ህዝብን በማሳተፍ በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአፈር ለምነትን በማሳደግ ምርት እና ምርታማነት እንዲጨምር ማስቻሉን ገልጸዋል። በሀገሪቱ 135 ገባሮች (ሳብ ቤዝን) ያሏቸው 12 ትላልቅ (ቤዝን) ተፋሰሶች መኖራቸውን የጠቀሱት መሪ ስራ አስፈጻሚው፤ አሁን ላይ ተጨማሪ 8 ሺህ 903 ታላላቅ ተፋሰሶች ተለይተው በመልማት ላይ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡ በማህበረሰብ ደረጃ ተለይተው በመልማት ላይ በሚገኙ 197 ሺህ 843 አነስተኛ ተፋሰሶች በየዓመቱ ስነ አካላዊና ስነ ህይወታዊ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡   በዚህም በመንግስትና በህብረተሰብ ተሳትፎ 33 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ መልሶ የማልማት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። የበጋ የተፋሰስ ስራ የሚከናወንባቸው ቦታዎችን፣ ቀያሽ አርሶ አደሮችና ለስራው የሚያገለግሉ የእርሻ መሳሪያዎችን የመለየት ስራ በመጠናቀቅ ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡
ዘርፉ ለብልፅግና ጉዞው ስኬታማነት እያበረከተ ያለውን የላቀ አስተዋጽኦ አጠናክሮ ቀጥሏል
Nov 14, 2025 53
ባሕርዳር፤ ሕዳር 5/2018(ኢዜአ)፡-የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፉ በኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ስኬታማነት እያበረከተ ያለውን የላቀ አስተዋጽኦ ይበልጥ አጠናክሮ መቀጠሉን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትሩ ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ የ2018 ሩብ የበጀት ዓመት የዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ መድረክ በባሕር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው።   በመድረኩ ላይ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) ፤ ዘርፉን በቴክኖሎጂ በማዘመን በሁሉም መስክ ስኬቶችን እያስመዘገበ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በሀገሪቱ በግብርናው፣በማዕድን፣ በቱሪዝም፣ በቴክኖሎጂ ልማትና መሰል እድገት ተኮር ዘርፎች ስኬታማነት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፉ አይተኬ ሚናውን እየተወጣ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም በውሃ፣ በአየርና በየብስ ተደራሽነትን የማሳደግና ዘመናዊነትን የማስፋት ስራ በልዩ ትኩረት እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ዘርፋ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እንዲሳካ አበክሮ በመስራት የሀገር አለኝታነቱን በተግባር አረጋግጧል ብለዋል። በሀገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያ የሆነችውን ግዙፏ የጣናነሽ ቁጥር ሁለት ጀልባ ወደ ጣና ሀይቅ በማስገባት አገልግሎት መስጠት ማስቻሉን ጠቅሰው፤ ይህም የውሃ ላይ ትራንስፖርቱን ያዘመነ ነው ብለዋል። በሀገሪቱ የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን በማሳለጥ ተጨባጭ ውጤት የታየበት ዘርፍ መሆኑን ያመለከቱት ሚኒስትሩ፤ ዘርፉ በኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ ስኬታማነት እያበረከተ ያለውን አስተዋጽኦ ይበልጥ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፋ ጽሕፈት ቤት ሀላፊ ይርጋ ሲሳይ በበኩላቸው፤ በክልሉ ሰላምን ከማፅናት ባሻገር ታላላቅ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል።   በተለይም በባሕር ዳር፣ ጎንደር፣ ደሴ፣ ወልዲያ፣ ኮምቦልቻ፣ ደብረ ብርሃና ሌሎች ከተሞች ሰፋፊ የኮሪደር ልማት ስራ ማከናወን ተችሏል ብለዋል። ቀጣይም በሌሎች ከተሞች የማስፋት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፤ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፋን በቴክኖሎጂ የማዘመን ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ በቴክኖሎጂ ታግዞ ተደራሽነትን የማስፋት ስራ እየተከናወነ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ባለስልጣን ሀላፊ ዘውዱ ማለደ ናቸው።   በመድረኩ የፌዴራልና የክልሎች የዘርፍ አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
የገጠር አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እያገዙ ነው
Nov 14, 2025 69
ድሬዳዋ፣ ህዳር 5/2018(ኢዜአ) በድርዳዋ የገጠር አነስተኛ የመስኖ ፕሮጀክቶች በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ማገዛቸውን የአስተዳደሩ ግብርና ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ በሚሆን በጀት በአራቱም የገጠር ክላስተሮች የአነስተኛ መስኖና የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ግንባታ እያፋጠነ መሆኑን አመልክቷል። በቢሮው የውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፉአድ መሐመድ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፥ አገራዊ ለውጡን ተከትሎ አስተዳደሩ የገጠሩን ማህበረሰብ የልማት ጥያቄዎች በመመለስ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ ይገኛል። በዚህም በአነስተኛ መስኖ ፕሮጀክቶች ሲለማ የነበረን ማሳ ከ4 ሺህ 500 ሄክታር ወደ 8ሺህ 500 በማሳደግ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጥረት መደረጉን ገልጸዋል። እነዚህን ውጤቶች ለማስፋት ከግማሽ ቢሊየን ብር በላይ በጀት በመመደብ በአራቱም የአስተዳደሩ ገጠር ክላስተሮች የመጠጥ እና የአነስተኛ መስኖ ፕሮጀክቶች መፋጠናቸውን አክለዋል።   ለአብነት በአሰሊሶ ክላስተር በ153 ሚሊዮን ብር የተገነባው በፀሐይ ኃይል የሚሰራው የመጠጥ እና የአነስተኛ መስኖ ፕሮጀክት የአካባቢውን አርሶአደሮች ተጠቃሚ ማድረጉን አንስተዋል። ሌሎች በከፊል አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙት የመስኖ ፕሮጀክቶችም 500 ሄክታር መሬትን በመስኖ ማልማት ማስቻላቸውን ተናግረዋል። እንደ አቶ ፉአድ ገለፃ፥ አገራዊ ለውጡን ተከትሎ አስተዳደሩ ለገጠሩ ማህበረሰብ በሰጠው ትኩረት በተሰሩት የልማት ስራዎች የገጠር ቀበሌዎች የመጠጥ ውሃ እና 33ቱ ደግሞ የአነስተኛ መስኖ ተጠቃሚ ሆነዋል። የገጠሩ ማህበረሰብ ፕሮጀክቶችን በባለቤትነት ከመንከባከብ በተጨማሪ በቡድን እየተደራጀ በጉልበቱ እና በገንዘቡ ለመስኖ የሚጠቀምበትን የውሃ ጉድጓዶች በመቆፈር ፀጋዎቹን ወደ ልማት እያሻገረ መሆኑንም ተናግረዋል።   በገጠሩ ማህበረሰብ ትጋት ከተረጂነት ሙሉ በሙሉ ለመላቀቅና በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንደሚያስችል ኃላፊው ተናግረዋል። የድሬዳዋ ገጠር ክላስተሮች የአስተዳደሩን 96 ከመቶ በላይ የቆዳ ስፋትና አንድ ሶስተኛውን ህዝብ ያካተተ ቢሆንም መልክዓ ምድሩ ዝናብ አጠርና በረሃማ መሆኑን ተከትሎ ባለፉት ጊዜያት ማህበረሰቡ ለተረጂነት ሲጋለጥ መቆየቱ ይታወሳል። በአሁኑ ጊዜ ማህበረሰቡ ተረጂነትን በፍጥነት ወደ ታሪክ ለመቀየር እያደረገ የሚገኘው ትጋት ውጤት እያስገኘ መሆኑንም ነው የገለጹት።
በከብት ማድለብ ስራ ላይ የተሰማሩ አርሶአደሮች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ ነው
Nov 14, 2025 56
መቱ፤ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡- በከብት ማድለብ ስራ በመሰማራት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መሆናቸውን በኢሉባቦር ዞን የበቾ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ። ነዋሪዎቹ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በከብት ማድለብ ስራ በመሰማራት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ ነው። በበቾ ወረዳ የጉዲና ቀበሌ ነዋሪው አቶ አያና አደም በመንግስት የተቀረፁ የግብርና ልማት ፕሮግራሞችን በመተግበር የምግብ ዋስትናቸውን ማረጋገጥ መቻላቸውን ተናግረዋል። ከዚህ ጎን ለጎን በከብት ማድለብ ስራ በመሰማራት ኢኮኖሚያዊ አቅማቸውን ለማሳደግ በሚያደርጉት ጥረት በዓመት ከ50 እስከ 60 በሬዎችን አደልበው ለገበያ በማቅረብ ተጨማሪ ገቢ ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል።   በዚሁ ወረዳ የጉዲና ሶር ቀበሌ ነዋሪዎቹ አቶ አብዲሳ ሆማ እና አቶ በላቸው ሆማ በበኩላቸው መንግስት በፈጠረላቸው ግንዛቤ በከብት ማድለብ ስራ ተሰማርተው ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። የመኖ አቅርቦቱን ከግብርና ስራቸው ጋር በማስተሳሰር ያደለቧቸውን ከብቶች በዓመት እስከ ሶስትና አራት ዙሮች ለገበያ ማቅረባቸውን አውስተዋል። በዚህም ጥሩ ገቢ በማግኘት የኢኮኖሚ አቅማቸውን በማሳደግ ሰባት ሚሊዮን ብር ካፒታል በማፍራት ወደ ኢንቨስትመንት እንደተሸጋገሩ ገልጸዋል።   የኢሉባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አወል መሐመድ በበኩላቸው፤ በዞኑ 1 ነጥብ 4 ሚሊዮን የሚሆኑ የዳልጋ ከብቶች መኖራቸውን ጠቁመው ከዞኑ የእንስሳት ሀብት ተጠቃሚ ለመሆን በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የእንስሳቱን ምርታማነት ከማሳደግ ባለፈ የመኖ አቅርቦትና አርሶ አደሩ ከብቶችን አደልቦ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚነቱን ለማሳደግ የቅርብ ክትትል መደረጉን አንስተዋል። በዚህም አርሶ አደሩ በየዓመቱ ከ240 ሺህ በላይ ከብቶችን አድልቦ ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ማሳደጉን ተናግረዋል። በከብት ማድለብ ስራው በመሳተፍም በርካታ አርሶ አደሮች የኢኮኖሚ አቅማቸው ከማሳደግ አልፈው ሀብት በማፍራት ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገር መቻላቸውን አስረድተዋል።
በጋምቤላ ከተማ የተጀመረው የኮሪደር ልማት እየተፋጠነ ነው
Nov 14, 2025 38
ጋምቤላ፤ ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ከተማ የተጀመረውን የኮሪደር ልማት በፍጥነት በማጠናቀቅ ከተማዋን ለነዋሪዎቿ የተመቸችና የቱሪዝም መስህብ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ። የጋምቤላ ከተማ ለቱሪስት መዳረሻ በሚሆኑ የተፈጥሮ ፀጋዎች ተከባ የምትገኝ ሲሆን፤ በተለይም ከተማዋን ለሁለት ከፍሎ የሚያልፈው የባሮ ወንዝ ለከተማዋ ልዩ ውበትና ድምቀት የሚያጎናጽፍ እንደሆነ ተመልክቷል።   የከተማዋ አስተዳደር ከንቲባ ቱት ጂክ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የጋምቤላን ውበትና ፀጋን ይበልጥ ለማጉላት እንደ ሀገር የተጀመረው የኮሪደር ልማት ኢኒሼቲቨ በከተማዋም እየተተገበረ ይገኛል። በጋምቤላ ከተማ የተጀመረውን የኮሪደር ልማት በማፋጠን ከተማዋን ለነዋሪውና ለጎብኚዎች ምቹ ለማድረግ እየተከናወነ ያለው ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል፡፡   በከተማው በመጀመሪያው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ከ14 ኪሎ ሜትር በላይ ርዝመት ያላቸው አራት ዋና ዋና መንገዶችን ለማልማት የተያዘውን ግብ ለማሳካት ስራው በመፋጠን ላይ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡ ነዋሪውም ለኮሪደር ልማቱ ስኬታማነት ሀብት ከማሰባሰብ ጀምሮ እያሳየ ያለው ትብብር እና ድጋፍ የሚደነቅ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ ከኮሪደር ልማቱ ጎን ለጎን የከተማውን የውስጥ ለውስጥ መንገዶች ደረጃ በማሻሻል የሕዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል።   የተጀመረው የኮሪደር ልማት ከተማዋን ጽዱ፣ ውብና ማራኪ ከማድረግ ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል እየፈጠረ መሆኑንም ከንቲባው አስታውቀዋል፡፡ በኮሪደር ልማቱ የስራ እድል ከተፈጠረላቸው መካከል ወጣት አጥናፉ አሰፋ ፤ የኮሪደር ልማቱ በፈጠረለት የስራ እድል ራሱንና የቤተሰቦቹን ህይወት መቀየሩን ነው የተናገረው።   የኮሪደር ልማቱ ከተማውን ይበልጥ ውብና ሳቢ ከማድረግ ባለፈ አዳዲስ ሙያዎችን እንዲለምዱ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸውም ወጣቶቹ ገልጸዋል።
በደብረ ብርሃን ከተማ ለአምራች ኢንዱስትሪ ምቹ የኢንቨስትመንት ምኅዳር ተፈጥሯል
Nov 14, 2025 58
አዲስ አበባ፤ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ለአምራች ኢንዱስትሪ የተፈጠረው ምቹ ምኅዳር ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው በደብረብርሃን ከተማ በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ አምራቾች ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞንና ደብረ ብርሃን ከተማ በአምራች ኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት የተሰማሩ ድርጅቶችን መጎኘታቸው ይታወሳል።   በዚሁ ወቅትም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ በደብረ ብርሃን ከተማ የተገነባውን የብራውን ፉድ የብቅልና አልሚ ምግብ ማምረቻ ፋብሪካ መርቀው ስራ አስጀምረዋል። የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሰሜን ሸዋ ዞንና ደብረ ብርሃን ከተማ የአምራች ኢንዱስትሪዎች የመስክ ምልከታ የምርታማነትን ለማሳደግ መነሳሳትን እንደሚፈጥር የድርጅት ስራ አስኪያጆች ገለጸዋል።   በበላይነህ ክንዴ ቢዝነስ ግሩፕ የፊቤላ ደብረ ብረሃን መኪና መገጣጠሚያ ስራ አስኪያጅ መሐመድ አሕመድ፥ የደረቅና ፈሳሽ ጭነት እንዲሁም በኤሌክትሪክ የሚሰሩ የከተማ ባሶችን እየገጣጠሙ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   በቀን አስራ ሁለት፤ በዓመት 1 ሺህ ተሽከርካሪ የማምረት አቅም ያለው የፊቤላ ደብረ ብርሃን መኪና መገጣጠሚያ የነዳጅ ወጪን በማስቀረት ለትራንስፖርት ዘርፍ ከፍተኛ እገዛ እያደረገ ነው ብለዋል። ዓለም የደረሰበትን ቴክኖሎጂን በመጠቀም ጥራት ያላቸው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች እየተመረቱ ነው ብለዋል። በመኪና መገጣጠሚያ ፋብሪካው የሥራ ዕድል የተፈጠረላቸው ዜጎችም በቴክኖሎጂ የዕውቀትና ክህሎት ሽግግር ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የዴዴቦ ቦትል ፋብሪካ ሥራ አስኪያጅ ደሳለኝ ፈንታ፥ ብርጭቆ፣የምግብ ማሸጊያ ጃር፣ የለስላሳና የቢራ ጠርሙሶችን ለማምረት በዝግጅት ላይ መሆናቸውን አስታውቀዋል።   በቀን ከ450 ሺህ እስከ 500 ሺህ ጠርሙስ የማምረት አቅም ያለው ፋብሪካው 86 ከመቶ የሀገር ውስጥ ጥሬ ዕቃን በመጠቀም ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን ለመተካት እንደሚሰራ ገልጸዋል። ፋብሪካው ወደ ስራ ሲገባ በ24 ሰዓት የምርት ሂደት በርካታ ዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል። የደብረ ብርሃ ከተማ ለአምራች ኢንዱስትሪ ያላት ምቹ ምኅዳርና የተደረገላቸው የሚገኙ ድጋፍ በኢንቨስትመንት የሚሰማሩበትን ዕድል እንደፈጠረላቸው አስረድተዋል።
ከተሞችን ለኑሮ ምቹ የማድረግ ተግባር በጥናትና ምርምር እየተደገፈ ነው 
Nov 14, 2025 61
ጭሮ ፤ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ከተሞችን ዘመናዊና ለኑሮ ምቹ የማድረግ እንቅስቃሴ በጥናትና ምርምር እየተደገፈ መሆኑን የክልሉ ከተማ ፕላን ኢንስቲትዩት ገለጸ፡፡ ኢንስቲትዩቱ በክልሉ ከተሞች ላይ ያካሄደውን ችግር ፈቺ የጥናት እና ምርምር ስራዎችን ለባለድርሻ አካላት ያቀረበበት ሲምፖዝየም በጭሮ ከተማ ተካሂዷል፡፡ በዚሁ ወቅት የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ መርጋ ኦሊቃ እንዳሉት የክልሉ የከተማ ፕላን ኢንስቲትዩት ከተሞች ዘመናዊ ፕላን እንዲኖራቸው እና በሁሉም ረገድ ያሉባቸውን ችግሮች ለመፍታት በጥናት እና ምርምር የታገዘ ድጋፍ እያደረገ ነው፡፡   ኢንስቲትዩቱ በክልሉ ለሚገኙ አብዛኛዎቹ ከተሞች ዘመናዊና ደረጃውን የጠበቀ ፕላን ማዘጋጀቱን አንስተው በጎርፍ ተጋላጭነት፣ በአካባቢ ልማት እና አረንጓዴ ልማት ላይ ያተኮሩ ሶስት ችግር ፈቺ የጥናት ስራዎች በ14 ከተሞች ላይ መከናወናቸውንም አመልክተዋል፡፡ ኢንስቲትዩቱ ለከተሞቹ ዘመናዊ ፕላን ከማዘጋጀት ባለፈም ለየከተሞቹ አመራርና ባለሙያዎች ድጋፍና ስልጠና በመስጠት ላይ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ የክልሉን ከተሞች በዘመናዊ መልኩ ለማልማት የተጀመረውን ጥረት በማገዝ ከተሞቹ ሙሉ ለሙሉ ደረጃውን የጠበቀ ፕላን እንዲኖራቸው ትኩረት ተሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በጭሮ ከተማ የተካሄደው ሲምፖዝየምም የጥናትና ምርምሮቹን ግኝት በከተሞቹ ለሚገኙ ባለድርሻ አካላት ለማቅረብ ነው ብለዋል፡፡ በመቱ፣ ገለምሶ፣ አሰላ እና ባቢሌ ከተሞች ላይ በማተኮር በከተሞች መኖሪያ አካባቢ በተካሄደው ጥናት በከተሞቹ የፕላን አዘገጃጀት አሳታፊ ያለመሆን እንደ ዋነኛ ችግር የታየ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተመሳሳይ በበዴሳ፣ ሳጉሬ፣ ዴራ፣ ቡሌ ሆራ እና ቢሾፍቱ ከተሞች የከተሞች አረንጓዴ ልማት ላይ ያተኮሩ የጥናት ስራዎች ተከናውነው መልካም ጅምሮች እንዳለ ተለይቷል ብለዋል። የጥናት ስራውን ካከናወኑ መካከል በኦሮሚያ ስቴት ዩኒቨርሲቲ መምህር ንጉሴ ደበሌ (ዶ/ር) እንዳሉት ቀደም ሲል የተገነቡ ግንባታዎች በተገቢው እና ደረጃውን በጠበቀ ፕላን ባለመገንባታቸው ከተሞች ዘመናዊና ምቹ እንዳይሆኑ አድርጓል፡፡   በአሁኑ ወቅት መንግስት ከተሞችን ዘመናዊና ለኑሮ ተስማሚ ለማድረግ የጀመረውን ጥረት የሚያግዝ ችግር ፈቺ የጥናት ስራ ማከናወናቸውን አመልክተዋል፡፡ መንግስት ከተሞችን በዘመናዊ መልኩ ለማልማት የጀመረው ጥረት የአገሪቱን ብልጽግና የሚያረጋግጥ በመሆኑ ባለድርሻ አካላት ሊደግፉት ይገባል ብለዋል። የገለምሶ ከተማ ከንቲባ አቶ መሀመድ አብደላ በበኩላቸው በኢንስቲትዩቱ የተከናወነው የጥናት ስራ በርካታ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን የጠቆመና ከተሞችን ለማዘመን እየተደረገ ያለውን ጥረት የሚያግዝ እንደሆነ አንስተዋል፡፡   በሲምፖዝየሙ ላይ ከተለያዩ የክልሉ ከተሞች የተውጣጡ ባለሙያዎች እንዲሁም የጭሮ ከተማ ነዋሪዎች ተሳትፈዋል፡፡
የቀኑ መከበር የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን ለማሳደግ የጎላ አስተዋፅኦ አለው
Nov 14, 2025 88
አዲስ አበባ፤ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡-የብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን መከበር የሕዝቦችን ትሥሥር ለማጎልበት፣የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን ለማሳደግ፣የቱሪዝም መሠረተ ልማቶችን ለማልማት እና ለማስተዋወቅ የጎላ አስተዋፅኦ እንዳለው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ፡፡ ቀኑ በየዓመቱ መከበሩ፤ የህዝቦች ትስስርን በማጠናከር እና በማጎልበት ህብረ-ብሄራዊ አንድነት በጠንካራ መሰረት ላይ እንዲገነባ ከፍ ያለ ፋይዳ እንዳለውም ጠቁመዋል። 20ኛው የብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በፌዴሬሽን ምክር ቤት አስተባባሪነት እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አስተናጋጅነት "ዴሞክራሲያዊ መግባባት ለህብረ ብሄራዊ አንድነት" በሚል መሪ ሃሳብ በሆሳዕና ከተማ በተለያዩ ዝግጅቶች ይከበራል ። ቀኑን ዲሞክራሲያዊ አንድነት እንዲጠናከር እና ኅብረብሔራዊ አንድነት እንዲጎለብት በሚያስችሉ ተግባራት ለማክበር በቂ ዝግጅት መደረጉን ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በሰጡት መግለጫ አስታውቀዋል። ርዕሰ መስተዳደሩ በመግለጫቸው የቀኑ መከበር ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች እርስ በእርስ እንዲተዋወቁና ህብረ ብሄራዊ አንድነት እንዲጠናከር ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑን አንስተዋል። የልማት ኢኒሸቲቮችን በላቀ ፍጥነትና ጥራት ለማከናወን እድል መፍጠሩን እንዲሁም ኢንቨስትመንት እንዲስፋፋ እና የከተሞች እድገትን እውን በማድረግ የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አስተዋፅኦ አለው ሲሉም ተናግረዋል። በዓሉ በክልሉ የሚገኙ ታሪካዊ፣ ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ የቱሪስት መዳረሻዎችን፣ ፀጋዎችን እና የኢንቨስትመንት አማራጮችን ለማስተዋወቅ ትልቅ እድል እንደሚፈጥር ጠቁመዋል ። ከተሞችን የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ በተያዘው አገራዊ አቅጣጫ በመታገዝ በክልሉ በከፍተኛ ህዝባዊ ተሳትፎ የኮሪደር ልማት እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። ክልሉን የሰላም ተምሳሌት ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አስተማማኝ ሰላም መፍጠር መቻሉን አስታውቀዋል። 20ኛው የብሔር ብሔረሰቦች እና ህዝቦች ቀን ታላቁ የህዳሴ ግድብ ተጠናቆ በተመረቀበት ማግስትና ኢትዮጵያውያን በሀገራዊ አጀንዳዎች በጋራ በቆምንበት ወሳኝ የታሪክ ምዕራፍ ላይ የሚከበር በመሆኑ ልዩ ያደርገዋል ሲሉም ተናግረዋል፡፡ የቀኑ መከበር የሕዝቦችን ትሥሥር ለማጎልበት፣ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴን ለማሳደግ፣ የቱሪዝም መሠረተ ልማቶችን ለማልማት እና ለማስተዋወቅ የጎላ አስተዋፅኦ እንዳለውም ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም