ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ኢትዮጵያ በሀገር ውስጥ ምርት እና የገንዘብ የመግዛት አቅም በምስራቅ አፍሪካ የቀዳሚነቱን ስፍራ ይዛለች - አይኤምኤፍ
Jul 8, 2026 34
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- ኢትዮጵያ በአጠቃላይ በሀገር ውስጥ ምርት (ጂዲፒ) እና በገንዘብ የመግዛት አቅም በምስራቅ አፍሪካ በቀዳሚነት ስፍራ ላይ እንደምትገኝ የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) አስታወቀ። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) በምስራቅ አፍሪካ የሚገኙ 19 ሀገራትን የገንዘብ የመግዛት አቅም (PPP) መሠረት በማድረግ እ.ኤ.አ. በግንቦት 2026 ባወጣው ይፋዊ መረጃ መሠረት፣ የኢትዮጵያ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት (GDP በPPP) 558.93 ቢሊዮን ዶላር በመድረስ በምስራቅ አፍሪካ አንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ኢትዮጵያን በመከተል ኬንያ በ435.21 ቢሊየን ዶላር ሁለተኛ፣ ታንዛኒያ ደግሞ በ320.88 ቢሊየን ዶላር ሦስተኛ ደረጃን ይዘዋል። የኢትዮጵያ፣ ኬንያ እና ታንዛኒያ ምጣኔ ሀብት በአንድ ላይ ሲደመር 1.35 ትሪሊየን ዶላር የደረሰ ሲሆን፣ ይህም ቀሪዎቹ 16 የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት በድምሩ ካላቸው አጠቃላይ የኢኮኖሚ መጠን በእጅጉ የሚበልጥ መሆኑ የኢትዮጵያን እና የጎረቤቶቿን የገበያ ግዙፍነት ያሳያል። ከእነዚህ ግንባር ቀደም ሀገራት በመቀጠል ዩጋንዳ፣ ሱዳን፣ ዛምቢያ እና ዚምባብዌ ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ያለውን የምጣኔ ሀብት ደረጃ ይዘዋል። ማዳጋስካር፣ ሩዋንዳ፣ ሞዛምቢክ፣ ማላዊ፣ ሞሪሸስ፣ ሶማሊያ፣ ብሩንዲ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ጅቡቲ፣ ኤርትራ እና ሲሸልስ ደግሞ በቅደም ተከተል ቀጣዮቹ ደረጃዎች ላይ ተቀምጠዋል። በአንጻሩ ኮሞሮስ በ3.43 ቢሊዮን ዶላር የመጨረሻው 19ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች።
በደቡብ ወሎ ዞን በግብርናው ዘርፍ የተገኘው አበረታች ውጤት ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jul 8, 2026 96
ደሴ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በደቡብ ወሎ ዞን በግብርናው ዘርፍ ቴክኖሎጂንና አዳዲስ አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ የተገኘው አበረታች ውጤት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮነን ገለፁ። በዞኑ 15 የእርሻ ትራክተሮች ለአርሶ አደሩ ተከፋፍለዋል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሊ መኮነን በርክክቡ ወቅት እንደገለጹት፤ በዞኑ ባለፉት የለውጥ ዓመታት ግብርናውን በማዘመን ምርታማነትን ለማሳደግ የተደረገው ጥረት አበረታች ውጤት ተመዘግቦበታል። ዞኑ በሜካናይዜሽን ለሚካሄድ የሰብል ልማት ምቹ መሆኑን ጠቁመው፣ እየተመዘገበ ያለውን ውጤት ለማስቀጠልም 15 የእርሻ ትራክተሮችን ለወረዳዎች ማስረከብ መቻሉን አስረድተዋል። በዚህም በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ጥራትና ብዛት ያለው ምርት በማምረት ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው፣ በዞኑ ግብርናውን ከኋላ ቀር አሰራር በማውጣት ወደ ዘመናዊ የአስተራረስ በዘዴ በመከተል ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው። በዚህም አርሶ አደሩ የምግብ ዋስትናውን ከማረጋገጥ ባለፈ ለኢንዱስትሪ ግብዓትና ለገበያ የሚተርፍ ምርት ማምረት የሚያስችል አቅም መፍጠሩን ተናግረዋል። ይህም የምርት ማሳደጊያ ቴክኖሎጂዎችንና አዳዲስ አሰራሮችን በተገቢው ሁኔታ በመተግበር የመጣ ውጤት መሆኑን አስረድተዋል። የመጣውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠልም ዛሬ የተሰራጩትን ጨምሮ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 37 የእርሻ ትራክተሮችን በማሰራጨት በአጠቃላይ በዞኑ ያሉ የትራክተሮች ቁጥርን 89 መድረሱን አረጋግጠዋል። "በዘመናዊና የተሻሻለ የግብርና አሰራር ምርታማነትን በማሳደግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ተችሏል" ያሉት ደግሞ የለጋምቦ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሁሴን ሙላት ናቸው። አርሶ አደሩ ሜካናይዜሽን አሰራርን እየተላመደ በመምጣቱ የቴክኖሎጂ ጥያቄው መስፋቱን ጠቁመው፣ ዛሬ የተረከቧቸውን ሁለቱን ጨምሮ 15 ትራክተሮች በስራ ላይ እንደሚገኙ አስገንዝበዋል። በርክክቡ ወቅት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር)፤የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ደረጀ ማንደፍሮ እና ሌሎች አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ ለዘላቂ ሰላምና የልማት ስራዎች ስኬት የመንግስትን ቀጣይነት ያለው ቁርጠኝነት ያረጋገጠ ነው
Jul 8, 2026 74
ሰመራ፤ ሐምሌ 1/2018(ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በትላንትናው ዕለት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰጡት ማብራሪያ ለዘላቂ ሰላምና የልማት ስራዎች ስኬት የመንግስትን ቀጣይነት ያለው ትጋትና ቁርጠኝነት ያረጋገጠ መሆኑን በአፋር ክልል የሰመራ ሎጊያ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በትናንትናው ዕለት ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ መስጠታቸው ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸውም መንግስት በተለይም ለዘላቂ ሰላም፣ ለንግግርና ውይይት ሁልጊዜም ዝግጁ መሆኑን አስረድተዋል። የግጭትና ጦርነት እሳቤ አውዳሚና ትርፍ የሌለው መሆኑን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚያስፈልገን ሰላም፣ ትብብር እና አብሮነት ነው ብለዋል። ከዚሁ ጋር በተገናኘ በአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያ ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ ለዘላቂ ሰላምና የልማት ስራዎች ስኬት የመንግስትን ቀጣይነት ያለው ትጋትና ቁርጠኝነት ያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል አቶ ዋሲሁን አያሌው፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምክር ቤት ተገኝተው የሰጡት ማብራሪያ ዘርፈ ብዙ ጉዳዮችን የዳሰሰ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የሰላም ጉዳይ ወሳኝ መሆኑን በማንሳት የግጭትና ጦርነት እሳቤ አውዳሚና ትርፍ የሌለው በመሆኑ የሰላም ጥረታችን ተጠናክሮ ይቀጥላል ማለታቸው መንግስት ለሰላም ያለውን ጽኑ አቋም ያረጋገጠ ነው ብለዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ማብራሪያ የትኛውንም ችግር በውይይትና በንግግር መፍታት አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት የሰጠ በመሆኑ ሁላችንም የሰላምን ጉዳይ የራሳችን አጀንዳ አድርገን መስራት አለብን ነው ያሉት። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ ወጣት ሙሳ መሐመድ በበኩሉ፥ ባለፉት አምስት ዓመታት ሁላችንንም ተጠቃሚ ያደረጉ በርካታ የልማት ሥራዎች ተሰርተዋል ይህንንም በበቂ ማሳያዎች መግለጽ ይቻላል ብሏል። በመሆኑም በልማት የተገኘውን ስኬት በሰላም ግንባታም በመድገም ለሁለንተናዊ እድገትና የጋራ ተጠቃሚነት መስራት ይገባናል ሲል ገልጿል። አገልግሎት አሰጣጥን ዲጂታላይዝ በማድረግ፣ በከተሞች አካባቢ ቀልጣፋ የአገልግሎት ተጠቃሚነትን በፍጥነት ማሳደግ መቻሉን የገለጹት ደግሞ አቶ ረምዚ ይማም ናቸው። የትምህርት ጥራትን በማረጋገጥ ረገድም አሁን ባለው ሁኔታ እየተከናወኑ ያሉት ሥራዎች አበረታች መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በትምህርት ዘርፉ በርካታ ሞዴል ትምህርት ቤቶች መገንባታቸን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሚገባ መግለጻቸውን ተናግረዋል።
በምዕራብ ወለጋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ470 በላይ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቅተዋል
Jul 8, 2026 81
ጊምቢ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የሕዝቡን የልማት ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ከ470 በላይ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት መብቃታቸውን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ተሊላ ተረፋ ገለጹ። ዋና አስተዳዳሪው እንደተናገሩት፤ ለአገልግሎት የበቁት እነዚህ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች የተገነቡት ከ2 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ነው። በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ተጠናቀው ወደ ሥራ ከገቡት የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች መካከል የንጹሕ መጠጥ ውኃ ተቋማት፣ የአነስተኛና ጥቃቅን ማኑፋክቸሪንግ ሼዶች፣ የመስኖ ልማት መሠረተ ልማቶች፣ የገጠርና የከተማ መንገዶች እንዲሁም የጤና ኬላዎች እና የትምህርት ተቋማት ናቸው ብለዋል። የእነዚህ ፕሮጀክቶች ወደ ሥራ መግባት በአካባቢው የሰፈነውን ሰላም ከማጽናት ባለፈ፣ ሕዝቡ ልማቱን በማፋጠን የራሱን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ እንቅስቃሴዎች በንቃት እንዲያሳልጥ ትልቅ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። የዞኑ ነዋሪዎች በበኩላቸው ፤ በአካባቢው የተገነቡት ፕሮጀክቶች የሕዝቡን የቆየ የመልማት ፍላጎት በትክክል የመለሱ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዞኑ የተገነቡት የትምህርትና ጤና ተቋማት በቅርበት አገልግሎት እንድናገኝ እያስቻሉን ነው፤ ይህም ገንዘብና ጉልበታችንን በመቆጠብ በሌሎች የልማት ሥራዎች ላይ እንድንተጋ አግዞናል ብለዋል። እንዲሁም በአካባቢያችን የተገነቡ የመንገድ መሰረተ ልማቶች ምርታችንን በቀላሉ ወደ ገበያ በማድረስ ተጠቃሚ እንድንሆን እያገዘን ነው ሲሉም ተናግረዋል፡፡ በቀጣይም የአካባቢያችንን ሰላምና ልማት ዘላቂ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከምንጊዜውም በላይ የበኩላችንን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ ነን ብለዋል።
በሐረሪ ክልል በኮሪደር ልማቱ የተከናወኑት የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች ጎብኚዎችን እየሳቡ ነው
Jul 8, 2026 69
ሐረር፤ ሐምሌ 1/2018(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል በኮሪደር ልማቱ የተከናወኑት የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ተግባራት የቱሪስቶችን ፍሰት በከፍተኛ ሁኔታ እያሳደጉ መሆኑን በክልሉ በአስጎብኚነት የተሰማሩ ባለሙያዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “ቱሪዝም አዲሱ የኢኮኖሚ ሞተር!” በሚል ሰሞኑን በሰጡት ማብራሪያ በዘርፉ የተከናወኑ ተግባራትንና የመጡ ውጤቶችን አንስተዋል። የብዝሃ የኢኮኖሚ አማራጮችን መሰረት አድርጎ በመስራት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ የተመዘገበውን ስኬት በማሳያነት አቅርበዋል። በሐረር የሚገኙ ጥንታዊ፣ ሃይማኖታዊና ታሪካዊ ቅርሶች እድሳትና የኮሪደር ልማትና ስራዎች ለቱሪዝም ዘርፉ እድገትና ማንሰራራት ትልቅ አቅም ከመሆናቸው ባለፈ ጎብኚዎችን እየሳቡ መሆኑ ተገልጿል። የዘመናት ዕድሜ ያላቸው እነዚህ ቅርሶችን ከተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ አደጋዎች ለመታደግ በክልሉ መንግሥትና ባለድርሻ አካላት አማካኝነት የተቀናጀ የኮሪደር ልማት፣ የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራ ሲከናወን ቆይቷል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የጀጎልን ታሪካዊ ይዘት ሳይለቁ የተከናወኑ የጥገናና የማደስ ሥራዎች፣ የቱሪስት መናኸሪያዎችን የማስዋብ እንዲሁም የከተማዋን የምሽት ገጽታ የሚቀይሩ የኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች የቅርሶቹን ዕድሜ ከማራዘም ባለፈ ለጎብኚዎች ምቹና ሳቢ አካባቢን መፍጠር ችለዋል። ይህ አቀራረብ በተለይ የውጭና የሀገር ውስጥ ቱሪስቶች በከተማዋ የሚኖራቸውን ቆይታ እንዲያራዝሙና በባህላዊ እሴቶች ላይ ያላቸውን ልምድ እንዲያበለጽጉ ትልቅ ዕድል ፈጥሯል። የቅርስ ጥበቃና ማሻሻያ ሥራዎቹ የክልሉን የቱሪዝም ገቢ ከማሳደግ ባለፈ፣ በቀጥታ በአስጎብኚነት፣ በሆቴል አገልግሎትና በባህላዊ እደ-ጥበብ ምርቶች ሽያጭ ላይ ለተሰማሩ የአካባቢው ማህበረሰብ አባላት ሰፊ የሥራ ዕድልና የገቢ ምንጭ በመሆን የላቀ ፋይዳ እያበረከተ ይገኛል። በክልሉ በአስጎብኚ ስራ የተሰማራው ሐይሉ ጋሻው እንደሚገልጸው፤ የጀጎል ዓለምአቀፍ ቅርስን ጨምሮ በከተማና ገጠር ወረዳ የሚገኙ ታሪካዊና ጥንታዊ ቅርሶች የጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች ተሰርተዋል። እነዚህ የቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች እንዲሁም ሸዋል ኢድን ጨምሮ የሚከናወኑ ክብረ በዓላት የሀገር ውስጥም ሆነ የውጪ ጎብኚዎችን በመሳብ በኩል አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም የቱሪዝም ዘርፉን ለማጎልበት የክልሉ መንግስት በተለያዩ አማራጮች ያከናወነው የማስተዋወቅ ስራ ባለሀብቶች በከተማው ሪዞርቶችና ሆቴሎች እንዲገነቡ እድል መፍጠሩንም ተናግሯል። እንዲሁም በዘርፉ ለተሰማሩ ባለሙያዎች እየተሰጡ የሚገኙ ስልጠናዎችም ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ጠቁመዋል። ሌላው አስጎብኚ ቴዎድሮስ በላይ በበኩሉ፤ በከተማው በኮሪደር ልማት የተከናወኑት ስራዎች በቱሪዝም ዘርፉ ላይ መነቃቃትን መፍጠሩንና ከተማዋን ውብና ጽዱ ከማድረግ ባለፈ ጎብኚው ተመልሶ እንዲመጣ እያስቻሉ መሆኑን ገልጸዋል። በኮሪደር ልማት የተከናወኑት ስራዎች ቅርሶች ተጠብቀው እንዲቆዩና ለትውልድ እንዲተላለፉ ያስቻሉ መሆኑ አመልክተዋል። በክልሉ ጎብኚው የሚያርፍባቸው ሆቴሎችና ሪዞርቶችን ከማስፋፋት አንጻር እየተከናወኑ የሚገኙ አበረታች ስራዎችም ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠቁመዋል። የሐረሪ ክልል የቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሳሚ አብዱልዋሲ፤ በክልሉ በቱሪዘም ዘርፍ በተሰጠው ትኩረት የቱሪዝም መስህቦችን በማልማት፣ የጎብኚዎችን ቆይታ በማራዘምና ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ አቅም በማሳደግ በኩል የተሻሉ ተግባራት መከናወናቸውን መግለጻቸው ይታወሳል።
በኢትዮጵያ እየተገነቡ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በማነቃቃትና በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያሳዩ ነው
Jul 8, 2026 142
አሶሳ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በኢትዮጵያ እየተገነቡ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በማነቃቃትና በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያሳዩ መሆኑን በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህር የሆኑት ሙሐመድ ኢብራሂም ገለጹ። ኢትዮጵያ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት የሀገሪቱን የረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ዕድገት ለማረጋገጥና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያስችሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ እየሰራች ትገኛለች። ከእነዚህም መካከል በታዳሽ ኃይል ማመንጫ፣ በታላላቅ የትራንስፖርት መሠረተ ልማቶች፣ በኢንዱስትሪ ፓርኮች እንዲሁም በከተማ ውበትና በኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች ሰፊ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ እየተገነቡ ይገኛሉ። እነዚህ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች በሚገነቡበት ወቅት በርካታ የሥራ ዕድሎችን በመፍጠር፣ የሀገር ውስጥ ምርታማነትን በማሳደግና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ረገድ የጎላ ሚና እንዳላቸው የዘርፉ ባለሙያዎች በተደጋጋሚ ይገልጻሉ። ትናንት በተካሄደው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ጀምራ በማጠናቀቅ ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት እያስመዘገበች መሆኑን ተናግረዋል። መንግሥት በአሁኑ ወቅት የጀመራቸውን ሜጋ ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት በማጠናቀቅ ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ ባለበት በዚህ ወቅት፣ የፕሮጀክቶቹ ተጨባጭ የኢኮኖሚ ፋይዳ በምሁራንና በባለሙያዎች ዘንድ ሰፊ ትኩረት እየተሰጠው ይገኛል። ፕሮጀክቶቹ የሕዝቡን የዕለት ተዕለት ኑሮ የሚያሻሽሉ እና የኢትዮጵያን ጀምሮ የመጨረስ አቅም በይፋ የሚያረጋግጡ እንደሆኑ አንስተዋል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህር የሆኑት ሙሐመድ ኢብራሂም እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በብዝሃ ዘርፍ ላይ ያተኮረ መሆኑ በሁሉም ዘርፎች ተመጣጣኝ የሆነ የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲመዘገብ አግዟል። በተለይም ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የሚያመነጩት ገቢ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በመደገፍ ረገድ ተጨባጭ ውጤት እያሳዩ እንደሆነ ጠቁመው፤ ይህም የሀገሪቷን ገቢ እና ወጪን በማስተካከል ጤናማ የኢኮኖሚ ዕድገት እንዲመዘገብ አድርጓል ብለዋል። ይህም የሀገሪቷ ዓመታዊ በጀት በየጊዜው ጭማሪ እንዲያሳይ እንዲሁም ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም እንዲያድግ አይነተኛ ሚና እንዳለው አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በማዕድን፣ በኢንዱስትሪ እና በአግሮ ኢንዱስትሪ ዘርፎች ያከናወነቻቸው የሪፎርም ተግባራት ሀገሪቱን በምስራቅ አፍሪካ ቀዳሚ የኢኮኖሚ ባለቤት እንደሚያደርጋትም ትልቅ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ "ብሪክስን" ጨምሮ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር የጀመረችው የንግድ ግንኙነት እና የወጪ ንግድ መጨመር የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ተወዳዳሪነት የሚያሳድግ እንደሆነም አንስተዋል።
ኢትዮጵያ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመተካት የሄደችበት መንገድ ተጨባጭ ለውጥ እያሳየ ነው - ምሁራን
Jul 8, 2026 146
ጅማ ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- ኢትዮጵያ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ የሚያስወጡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት ለመተካት የሄደችበት መንገድ ተጨባጭ ለውጥ እያሳየ መሆኑን ምሁራን ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ትላንት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በሰጡት ማብራሪያ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ለማስፋፋትና ለማዘመን ከተያዙ ቁልፍ ዘርፎች መካከል የኢንዱስትሪው ክፍለ-ኢኮኖሚ ዋነኛውና የትኩረት ማዕከል መሆኑን ጠቅሰዋል። ከለውጡ በፊት በሀገሪቱ የነበሩ ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ከ47 በመቶ በታች እንደነበር ጠቅሰው፤ ለዚህም እንደ ፋይናንስ፣ መሬትና የኃይል አቅርቦት ችግሮች በምክንያትነት ይጠቀሱ እንደነበር ገልጸዋል። ይህንን ችግር ለመቅረፍ መንግሥት ልዩ ኮሚቴ በማቋቋም እያንዳንዱን ኢንዱስትሪ በመጎብኘትና ችግሮቻቸውን በየደረጃው ለመፍታት ባደረገው የተቀናጀ ጥረት፣ ቀድሞ የነበሩ ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅማቸው ዛሬ ላይ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማለቱን ተናግረዋል፡፡ እያደጉ የመጡት የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪዎች በርካታ ምርቶችን በሰፊው በማምረት ከውጭ የሚገቡትን ምርቶች በሀገር ውስጥ ከመተካት ባለፈ፣ ወደ ውጭ የሚላከውን መጠን ከፍ አድርገውታል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የዘርፉ ምሁራን እንደገለጹት፤ መንግስት ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመተካት የሄደበት መንገድ ተጨባጭ ለውጥ እያሳየ ነው። በድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ የቢዝነስ እና ኢኮኖሚክስ ትምህርት ክፍል መምህር መስፍን መኮንን (ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ ባለፉት ዓመታት የውጭ ምንዛሬ እጥረት በትልቅ ተግዳሮትነት የቆየ ቢሆንም አሁን ላይ ግን ችግሩ በፍጥነት እየተቀረፈ ይገኛል። አዳዲስ የኢንዱስትሪ ፓርኮች መገንባታቸውና የማምረት አቅማቸው በየጊዜው እንዲያድግ በተደረገው ጥረት በኢትዮጵያ ታሪክ ከፍተኛ የሆነ የውጭ ምንዛሬ ማዳን ተችሏል ብለዋል። አክለውም ኢንዱስትሪዎች የሀገር ውስጥ ምርቶችን በቀላሉና በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ በማቅረብ የውጭ ምርቶችን እያስቀሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ለዚህም የጨርቃ ጨርቅና የቆዳ ውጤቶችን ለአብነት በማንሳት በዚህ ሂደት እያደገ የመጣውን የሀገሪቱን የዲጂታል የቴክኖሎጂ አቅም አጋዠ እንደነበርም ገልጸዋል። በተጨማሪም በምግብ ራስን ለመቻል ግብርናውን አዘምኖ በስፋት የማምረት ስራ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ መሆን የሚችል መሆኑን በመግለጽ፣ መንግስት በቀጣይ ይፋ ያደረጋቸውና እየሰራባቸው ያሉ ጉዳዮች ከዚህ የተሻለ ለውጥ እንደሚያመጡ ተናግረዋል። ከውጭ የሚገቡ መድኃኒቶችን አስቀርቶ በሀገር ውስጥ የማምረት አቅም እያደገ መምጣቱ፣ እንዲሁም የማዳበሪያ ፋብሪካ ያሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በመገንባት ከውጭ የሚገቡ የግብርና ግብዓቶችን ለማስቀረት የታቀደው ስራ ሀገሪቱን ወደፊት ተወዳዳሪ የሚያደርግ መሆንንም አስረድተዋል። በጅማ ዩኒቨርሲቲ የግብርና ምጣኔ ባለሙያ እና ተመራማሪ አደባ ገመቹ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ እንደ ስንዴ እና ሩዝ ያሉ ሰብሎችን በስፋት በማምረት ከውጭ የሚገባውን ምርት ለመቀነስና ለማስቀረት ስኬታማ ስራዎችን ማከናወኗን ገልጸዋል። ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ለመሸፈን የሚደረገው ጥረት ለወጣቶችና ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የስራ እድል እና የገበያ ትስስር እየፈጠረ ይገኛል ብለዋል። ቀደም ሲል በሀገር ውስጥ አይመረቱም ተብለው ይታሰቡ የነበሩ ምርቶች አሁን ላይ በጥራት እየተመረቱ መሆኑን በመጥቀስ ይህም የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎችንና ምርቶችን ማበረታታት በአቅርቦት ሰንሰለቱ ውስጥ ተጨማሪ የስራ እድሎችን ይፈጥራል ብለዋል። ይህ ጥረት በምግብ ምርት ላይ ያለንን የውጭ ሀገራት ጥገኝነት በመቀነስ፣ ሀገራዊ የምግብ ዋስትናን በአስተማማኝ ሁኔታ ለማረጋገጥ የሚረዳ በመሆኑ ኢትዮጵያ ለዚህ ተጨባጭ ስኬት በትጋት እየሰራች መሆኗን ገልጸዋል፡፡ የፋብሪካዎች መስፋፋትም ለዚህ ግብ መሳካት መሠረት እየሆኑ መምጣታቸውን ጠቁመዋል።
በባሌ ዞን በበጀት ዓመቱ ከ700 በላይ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት ተሸጋግረዋል
Jul 8, 2026 167
ሮቤ ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን በበጀት ዓመቱ 719 ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን የዞኑ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በተሰማሩበት የሥራ መስክ ውጤታማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩ አርሶ አደሮችና ማኅበራት የተደረገላቸው ማበረታቻ ለተሻለ ሥራ እንደሚያነሳሳቸው ገልጸዋል። የዞኑ ኢንቨስትመንትና ኢንዱስትሪ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መሐመድ ኢብሮ እንዳሉት፤ በዞኑ አርሶ አደሩ በተሰማራበት የሥራ መስክ ውጤታማ በመሆን መዋቅራዊ ሽግግር እንዲያደርግ ድጋፍ እየተደረገ ነው። በዚህም በዞኑ እየተገባደደ በሚገኘው የበጀት ዓመት 719 የሚሆኑ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች ከግብርና ወደ ኢንቨስትመንት በመሸጋገር የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው ሥራ ውስጥ መግባታቸውን አመልክተዋል። አርሶ አደሮቹና ኢንተርፕራይዞቹ ባለፉት ዓመታት በተሰማሩበት የሥራ መስክ ውጤታማ ከመሆን ባሻገር በነፍስ ወከፍ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገባቸውን ተናግረዋል። አርሶ አደሮቹና ማኅበራቱ ወደ ኢንቨስትመንት የተሸጋገሩት ባስመዘገቡት 2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ካፒታል መሆኑንም አስረድተዋል። የተሸጋገሩት አርሶ አደሮች ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ሲገቡ ከ14 ሺሕ 400 ለሚበልጡ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድል እንደሚፈጥሩም አክለዋል። ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች ከተሰማሩባቸው የሥራ መስኮች መካከል ማኑፋክቸሪንግ፣ አገልግሎት፣ ኢንዱስትሪና ሌሎችም ዘርፎች ይገኙበታል ብለዋል። ለተሸጋገሩ አርሶ አደሮች በተሰማሩበት የሥራ መስክ ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆኑ የመሬት አቅርቦትን ጨምሮ ሌሎች የብድርና የተለያዩ ማበረታቻዎች እንደሚደረግላቸውም ተናግረዋል። አቶ መሐመድ እንዳሉት፤ በዞኑ ባለፉት ዓመታት በግብርናው ዘርፍ የተከናወነው ውጤታማ ሥራ የተሸጋገሩ ግንባር ቀደም አርሶ አደሮች የግብርናው መስክ ሽግግር አዎንታዊ ማሳያዎች መሆናቸውን አክለዋል። ወደ ኢንቨስትመንት ከተሸጋገሩ አርሶ አደሮች መካከል አንዱ የሆኑት አቶ ኢብራሂም ከድር፤ በግብርና ሥራ በመሰማራት በሚያመርቱት ስንዴና ሌሎች ሰብሎች ውጤታማ በመሆን ወደ ኢንቨስትመንት መሸጋገራቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ወደ ምርጥ ዘር ብዜት ሥራ ለመሰማራት የሚያስችል የኢንቨስትመንት መሬት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት በግብርና ዘርፍ ባከናወኑት ውጤታማ ሥራ ከተሰጣቸው የእውቅና ሰርተፊኬት ባሻገር በኢንቨስትመንት ማበረታቻነት ያገኙት የመሥሪያ ቦታ ለተሻለ ስራ እንደሚያነሳሳቸው የገለጹት ደግሞ አቶ በያን መሐመድ ናቸው።
በክልሉ በዘመናዊ ግብርና የእንስሳት ሀብት ምርታማነትን የማሳደግ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jul 8, 2026 138
ደሴ ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- በአማራ ክልል በዘመናዊ ግብርና የእንስሳት ሀብት ምርታማነትን በማሳደግ ሁለንተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በምክትል ርዕስ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) ገለጹ። የክልሉ ግብርና ቢሮ "ዘመናዊ ግብርና ለሁለንተናዊ ልዕልና" በሚል መሪ ሐሳብ ያዘጋጀው የምክክር መድረክ በደሴ ከተማ ተካሒዷል። በምክትል ርዕስ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ድረስ ሳህሉ(ዶ/ር) እንደገለጹት፤የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ለወጭ ንግድና ለኢንዱስትሪ ግብአት የሚተርፍ ምርት ለማምረት ርብርብ እየተደረገ ነው። በዚህም በዘመናዊ አሰራር፣ የምርት ማሳደጊያ ግብአት በመጠቀም፣ በሜካናይዜሽንና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ በክልሉ በቴክኖሎጂ የተደገፈ በዘመናዊ ግብርናና እንስሳት ሀብት ልማት የተጀመረው ስራ ምርታማነትን በማሳደግ ሁለተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ መሰረት እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም በምርምር የታገዙ አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን ተግባራዊ በማድረግ ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት የሚበረታቱ ናቸው ብለዋል። አርሶ አደሩ የሚያገኘውን እርጥበት ተጠቅሞ ፈጥኖ የዘር ስራውን እንዲጀምር፣ ውሃ እንዲያሰባስብ ፣ ፈጥነው የሚደርሱና ድርቅን የሚቋቋሙ አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን እንዲጠቀም ማድረግ እንደሚያስፈልግ ነው ያመላከቱት ። ለዚህም መንግስት ምርታማነትን ለማሳደግ ቴክኖሎጂና ግብዓቶችን በስፋት እያቀረበ እንደሚገኝም ገልጸዋል። የአማራ ክልል እንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጋሻው ሙጨ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤የእንስሳት ዝርያን በማሻሻል በጥራት እንዲመረት ከማድረግ አኳያ አበረታች የሆኑ ውጤቶች ተመዝግበዋል ብለዋል። በተለይም በሌማት ትሩፋት የወተት፣ የስጋ ፣ የእንቁላል ፣ የማር ፣ የዓሳና የሌሎችንም ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ዜጎች ጥሪት እንዲያፈሩ ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ሲሉ ገልጸዋል። የደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ደመቀ አድማሱ በበኩላቸው፣ በዞኑ በምርምር የወጡ አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን በመጠቀም ምርታማነትን ለማሳደግ ዝግጅት እየተደረገ ነው ብለዋል። በተለይ ድርቅን የሚቋቋሙ፣ ምርታማና ፈጥነው የሚደርሱ ምርጥ ዘሮችን ለአርሶ አደሩ ለማቅረብ እንዲቻልም ሰፊ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የሰሜን ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ተገኝ አባተ በበኩላቸው፣ በተሻሻለ አሰራርና ቴክኖሎጂን በመጠቀም የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ንግድና ኢንቨስትመንት ፍሰትን በማሳደግ እመርታዊ ውጤት እያስገኘ ነው
Jul 7, 2026 481
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ንግድና ኢንቨስትመንት ፍሰትን በማሳደግ እመርታዊ ውጤት እያስገኘ መሆኑን በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ዮሐንስ ፋንታ ገለጹ። የኢትዮጵያ ንግድ ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ከፍተኛ የኤክስፖርትና የዲፕሎማሲ ፎረም የመንግስት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች፣ የሀገራት ዲፕሎማቶች፣ የኢትዮጵያ ላኪዎች፣ አምራቾችና ባለድርሻ አካላት መተገኙበት እየተካሄደ ነው። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ዮሐንስ ፋንታ በመድረኩ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ ተከታታይነት ያለው ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እያስመዘገበች ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ለጠንካራ የንግድ ኢንቨስትመንትና ለቀጣናዊ ትስስር ማዕከል ለመሆን ምቹ ሁኔታ ያላት መሆኗን ገልጸዋል። ይህም የወጪ ንግድን ለማጠናከርና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነቶችን ማጠናከር ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። ዲፕሎማሲ የኢኮኖሚ ግንኙነቶችንና አጋርነት የሚጠናከርበትና ዘላቂ ልማት በተግባር የሚረጋገጥበት ስትራቴጂያዊ መሣሪያ መሆኑንም አክለዋል። በዚህም መሰረት መንግሥት ኢትዮጵያን በንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ያላትን እምቅ ሀብቶች ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የማስተዋወቅ ስራውን አጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ንግድ ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ዋና ፀሀፊ ቀነኒሳ ለሚ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የፎረሙ ዋና ዓላማ የኢትዮጵያን የኤክስፖርት ምርቶች፣ አገልግሎቶችና የኢንቨስትመንት አማራጮች ለዓለም አቀፍ አጋሮች ማስተዋወቅ መሆኑን ተናግረዋል። መንግሥት የጀመረው የሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ለንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፉ የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ ለመዳሰስና ለባለሃብቶች ለማስተዋወቅ ፎረሙ ትልቅ ሚና እንደሚኖረው አስረድተዋል። የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት እና በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተዘጋጀው መድረክ የኢትዮጵያን ምርቶችና አገልግሎቶች በዓለም አቀፍ ገበያ ለማስተዋወቅ ጠንካራና ይበልጥ የተቀናጀ አሰራር ለመፍጠር ያግዛል ብለዋል።
በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚችል ግብርና በማጎልበት ተጨባጭ ውጤቶች ተገኝተዋል
Jul 7, 2026 206
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚችል ግብርና በማጎልበት ተጨባጭ ውጤቶች መገኘታቸውን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግሥታት (ኢጋድ) አባል አገራት የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚችል ግብርና ላይ ያተኮረ የሁለት ቀናት አውደ ጥናት እየተካሄደ ይገኛል። በአውደ ጥናቱ መክፈቻ ላይ በግብርና ሚኒስቴር የሚኒስትሩ አማካሪ ዜና ሀብተወልድ እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚችል ግብርና ለማስፋፋት በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛል። የመስኖ ስንዴ ልማት፣ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር፣ የአፈር መሸርሸርን መከላከልና ጤንነትን የመጠበቅ፣ የእንስሳት ምርታማነትን የማሻሻያና ሌሎች ስራዎችን ለአብነት ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚችል ግብርና ለማጎልበት የተገኙ ውጤቶች ለኢጋድ አባል ሀገራት ተሞክሮ የሚውሉ መሆናቸውን አመልክተው፤ በቀጣናው የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚችል የግብርና ልህቀት ማዕከል ለማቋቋም ግብዓት እንደሚሆን አንስተዋል። የአየር ንብረት ለውጥን የመቋቋም ስራዎች በአንድ ሀገር ብቻ የሚከናወን ሳይሆን የአገራት ቅንጅት የሚያስፈልግ በመሆኑ ከምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግሥታት (ኢጋድ) ጋር የሚከናወኑ ተግባራትን ለማጠናከር እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የኢጋድ አባል ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥን ከመቋቋም አኳያ ያሉበት ደረጃ ላይ ያተኮረ ጥናት መካሄዱን ገልጸዋል። በአውደ ጥናቱ ውይይት የሚቀርበው ጥናት የአባል አገራትን የአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና የልህቀት ማዕከላትን ለማቋቋም፣ ቀጣናዊ ትብብርን ለማጠናከር፣ የአየር ንብረት ተስማሚ ግብርናን የመቋቋም አቅምን ለመገንባት ወሳኝ ነው ብለዋል። በምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግሥታት (ኢጋድ) የግብርና እና አካባቢ ጥበቃ ዳይሬክተር ዳሄር ኤልሚ በመወከል የኢጋድ የፖሊሲና የምግብ ዋስትና ኤክስፐርት ሲልቪያ ሄንጋ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የአየር ንብረት ለውጥ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አምራች አርሶ አደሮችን እየጎዳ ይገኛል ። የሙቀት መጠን መጨመር፣ ድርቅ፣ የጎርፍ አደጋዎች፣ የመሬት መራቆት፣ የምግብ ዋስትናና ሌሎች ችግሮች የኢኮኖሚ እድገትን እና ዘላቂ ልማትን እያደናቀፉ ይገኛሉ ብለዋል። በመሆኑም፣ የመቋቋም አቅም ያለው ግብርና፣ ምርታማ እና ዘላቂ የምግብ ሥርዓትን ለመገንባት የአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ወሳኝ መሆኑን ነው የገለጹት። በሳይንስ፣ በማስረጃ እና ውጤታማ በሆኑ የእውቀት ሽግግር ላይ የተመሰረቱ ፈጠራ የታከለባቸው እና የተቀናጁ ቀጣናዊ ምላሾችን ይሻሉ ብለዋል። አውደ ጥናቱ የኢጋድ አባል አገራት የምግብ ሥርዓቶች የመቋቋም አቅም ፕሮግራም ውስጥ ትልቅ ምዕራፍ ነው፤ የቀጣናውን ተጨባጭ ሁኔታዎች በትክክል የሚያንፀባርቅ እና ወደ ተግባር ሊቀየሩ የሚችሉ ምክረ-ሃሳቦች እንዲሁም ቴክኒካዊ እውቀት ለማጎልበት ጉልህ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ የቀጣናውን የኃይል ትስስር ይበልጥ በማጠናከር የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቷን ለማረጋገጥ እየሰራች ነው
Jul 7, 2026 189
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የቀጣናውን የኃይል ትስስር ይበልጥ በማጠናከር የዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቷን ለማረጋገጥ እየሰራች መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) ገለጹ። የምሥራቅ አፍሪካ የኃይል ትስስር (EAPP) የቀጣናውን የኃይል ንግድ በይፋ ለማስጀመር የሚያስችልና አባል ሀገራትን መግባባት ላይ የሚያደርስ ልዩ ስብሰባ ማካሄድ ጀምሯል። ይህ መድረክ አባል ሀገራትን መግባባት ላይ ለማድረስና የቀጣናውን የኃይል ንግድ በይፋ ለመክፈት ያለመ ወሳኝ ምዕራፍ ነው። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ለምስራቅ አፍሪካ የምታቀርበው የኤሌክትሪክ ኃይል በቀጣናው አስተማማኝና ዘላቂ አቅርቦት ለመፍጠር የምታደርገውን ጥረት እንደሚያሳይ ገልጸዋል። ይህ የኃይል ትስስር ለኢትዮጵያ ትልቅ የገቢ ምንጭ ከመሆኑ ባለፈ፣ በአባል ሀገራቱ መካከል በፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ እና ባህላዊ ዘርፎች ጠንካራ መስተጋብር እንዲፈጠር እያደረገ ይገኛል ብለዋል። በአሁን ወቅት ይህንን ቀጣናዊ መስተጋብር ወደ አንድ የጋራ የአፍሪካ የኃይል ትስስር ለማሳደግ መጠነ-ሰፊ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ሚኒስትር ዴኤታው አስረድተዋል። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ዋና ሥራ አስፈፃሚ እና የምሥራቅ አፍሪካ የኃይል ትስስር (EAPP) ሊቀመንበር ኢንጂነር አሸብር ባልቻ፤ የኃይል ትስስሩ ለሀገር በርካታ ጥቅሞች እንዳሉት አብራርተዋል። የኢትዮጵያን ቀጣናዊ ተሰሚነትና የዲፕሎማሲ አቅም ከማሳደግ ባለፈ፤ ከኃይል ሽያጭ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ እያስቻላት መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአሁን ወቅት ከኬንያ፣ ሱዳን፣ ጂቡቲና ታንዛኒያ ጋር ስምምነት በመፍጠር ኃይል እያቀረበች መሆኗን ጠቁመዋል። ዋና ሥራ አስፈፃሚው አክለውም፤ በቀጣይም ከደቡብ ሱዳን እና ከሶማሊያ ጋር የኃይል ትስስር ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የብዝኅ-ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ ምርታማነትን በማሻሻል የዘርፎችን ውጤታማነት አሳድጓል
Jul 7, 2026 504
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የተከተለችው የብዝኅ-ዘርፍ ኢኮኖሚ ትግበራ ስኬታማ የሪፎርም ሥራዎች ምርታማነትን በማሳደግ የዘርፎችን ውጤታማነት ማሳደጉን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ተገኝተው፣ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት የሥራ አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም፤ መንግሥት የጀመራቸው አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እርምጃ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ተከታታይ ዕድገት እንዲያስመዘግብ ማስቻሉን ገልጸዋል። ግብርና 7 ነጥብ 7 በመቶ ዕድገት እንደሚመዘገብ ይጠበቃል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ዘንድሮ 29 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በማልማት 1 ነጥብ 3 ቢሊየን ኩንታል ምርት ተሰብስቧል ብለዋል። የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለማስፋፋትና ለማዘመን ከተያዙ ቁልፍ ዘርፎች መካከል የኢንዱስትሪው ክፍለ-ኢኮኖሚ ዋነኛውና የትኩረት ማዕከል መሆኑን ጠቅሰዋል። ከለውጡ በፊት በሀገሪቱ የነበሩ ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ከ47 በመቶ በታች የነበረው የማምረት አቅም አሁን ላይ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማለቱን ተናግረዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እፀገነት መንግስቱ እንዳሉት፤ በአምስት ዓመታት የምክር ቤት ዘመን ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ እመርታን አስመዝግባለች። በተጠናቀቀው የ2018 በጀት ዓመትም በብዝኅ ኢኮኖሚ ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራት የተኪ ምርት አቅምን በማሳደግ በወጪ ንግድ ጭምር ተጨባጭ ውጤት መገኘቱን ገልጸዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአመራር ቁርጠኝነት፣ የዜጎች ትብብርና የመሪነት ሚናም ኢትዮጵያ ላስመዘገበችው እመርታ ጉልህ አስተዋፅኦ ማበርከቱን አንስተዋል። በምክር ቤቱ የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አራሬ ሞሲሳ በበኩላቸው፤ ባለፉት አምስት ዓመታት በርካታ አዋጆች በማፅደቅ ጠንካራ የክትትልና ቁጥጥር የህዝብ ውክልና ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት ዓመታት በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊና ሌሎች የልማት ዘርፎች ውጤታማ ፕሮጀክቶች እንዲገነቡ በማስቻልና የከተማ ገፅታን በመቀየር በርካታ ስኬቶች መገኘታቸውን ተናግረዋል። የምክር ቤቱ አባል መስፍን እርካቤ፤ በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ጥያቄና ችግሮች ምላሽ እያገኙ ምርታማነት እያደገ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ባለፉት አምስት ዓመታት የገጠሟትን የውስጥና የውጭ ፈተናዎች ተቋቁማ በሁሉም ዘርፎች የተሻለ ውጤት አስመዝግባለች ያሉት ደግሞ የምክር ቤቱ አባል የሆኑት አቡኔ አለም ናቸው። የምክር ቤት አባላቶቹ እየተከናወኑ የሚገኙት ውጤታማ የልማት ተግባራት ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም ገልጸዋል።
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ግንባታቸው ተጠናቆ ወደ ሥራ የገቡ የልማት ተቋማት የህብረተሰቡን የልማት ጥያቄዎች የመለሱ ናቸው
Jul 7, 2026 126
ጭሮ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ጭሮ ከተማ ግንባታቸው ተጠናቆ ወደ ሥራ የገቡ የልማት ተቋማት የረጅም ጊዜ የልማት ጥያቄዎችን የመለሱ መሆናቸውን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። በከተማዋ ከ385 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የተለያዩ የልማት ፕሮጀክቶች በዛሬው ዕለት ተመርቀዋል። በፕሮጀክቶቹ ምረቃ ላይ የተገኙ የከተማዋ ነዋሪዎች ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ በአገልግሎት አሰጣጥ እና በመንገድ መሠረተ ልማት መስክ የነበሩባቸው ቅሬታዎችና ጥያቄዎች ምላሽ እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ አብደላ ኢስማኤል እንዳሉት፤ የመንግሥት አገልግሎት አሰጣጥ ያለመቀናጀትና ኋላቀር አሠራር ለእንግልትና ለተጨማሪ ወጪ ይዳርገን ነበር። አሁን ግን የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት በከተማዋ በመጀመሩ አገልግሎቶችን በአጭር ጊዜ እንድናገኝ ስለሚያደርገን ትልቅ ደስታ ተሰምቶናል ብለዋል። ሌላው ሼህ ኢስማኤል መሐመድ፣ በከተማዋ እየተካሄደ ያለው የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ደረጃቸውን የጠበቁ የውስጥ ለውስጥና ዋና መንገዶች እንዲኖሩ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ቀደም ሲል በከተማዋ ምንም የመዝናኛ ስፍራ አልነበረም፤ በአሁኑ ወቅት ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት የመንገድ ዳር መናፈሻ ስፍራዎችና የሳይንስ ካፌ በተለይ ወጣቶች ከአልባሌ ቦታዎች እንዲርቁና በቂ መዝናኛ እንዲያገኙ ያደርጋል ብለዋል። እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎች የከተማዋን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ የሚያሳድጉና የረጅም ዓመታት የልማት ችግሮችን የፈቱ መሆናቸውን የጠቀሱት ደግሞ አባገዳ አሽም አብደላ ናቸው። ወደ ፊትም ባላቸው አቅም ሁሉ ከልማቱ ጎን በመቆም የሚያደርጉትን ተሳትፎና ትብብር አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። የጭሮ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ መሐመድ ዑመር እንደገለጹት፤ በዛሬው ዕለት ተመርቀው ለአገልግሎት የበቁት ከ385 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ 17 የልማት ፕሮጀክቶች ናቸው። ፕሮጀክቶቹ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት፣ የኮሪደር ልማት፣ የመንገድ ዳር መዝናኛ ስፍራዎች እና የሳይንስ ካፌን ያካተቱ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከእነዚህም መካከል ከ100 ሚሊዮን ብር በሚሆን በጀት የተገነባው የአንድ ማዕከል አገልግሎት 68 የተለያዩ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ ማቅረብ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። የምዕራብ ሐረርጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ኢክራም ጠሀ በበኩላቸው፤ በዞኑ የሕብረተሰቡን ዘርፈ ብዙ የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ የተገነቡ 24 የልማት ፕሮጀክቶች በዚህ ዓመት ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን አስታውቀዋል። እነዚህ የልማት ፕሮጀክቶች የመንገድ መሠረተ ልማት፣ የውኃ ተቋማት፣ ድልድዮች እና በአርብቶ አደር ወረዳዎች የተገነቡ የውኃ ግድቦችን ያካተቱ መሆናቸውን አመልክተዋል። በተጨማሪም በዞኑ የጭሮን ከተማ ጨምሮ በመቻራ፣ ሂርና፣ ገለምሶ እና በዴሳ ከተሞችም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተደገፉ የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት መስጫዎች ለአገልግሎት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸው፤ ኅብረተሰቡ በአካባቢው እየተገነቡ ባሉ የልማት ፕሮጀክቶች ላይ ተሳትፎውን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል።
ባለፉት አምስት ዓመታት 40 ሺህ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቅተዋል
Jul 7, 2026 170
አዳማ፣ ሰኔ 30/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት አምስት ዓመታት በሀገር አቀፍ ደረጃ 40 ሺህ አዳዲስ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት መብቃታቸውን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። የሞጆ-አዳማ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክት የፌዴራልና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር አስፋው ዲንጋሞ ባስተላለፉት መልዕክት፣ ፕሮጀክቱ በርካታ ውስብስብ ፈተናዎችን አልፎ በተቀመጠለት ጊዜ መጠናቀቁን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱ ለ1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ህዝብ አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን አዳማ የንግድ፣ የኢንዱስትሪና የኢንቨስትመንት ማዕከል እንደመሆኗ፣ ፕሮጀክቱ ለሚቀጥሉት አስር ዓመታት የተሟላ አገልግሎት ይሰጣል ብለዋል። ባለፉት አምስት ዓመታት በሀገር አቀፍ ደረጃ 40 ሺህ አዳዲስ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች ተገንብተው ከ25 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በአሁኑ ወቅትም ከእነዚሁ ፕሮጀክቶች በተጨማሪ የጎዴና ቢቸና ከተሞች የውሃ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን አንስተዋል። የክልሉ መንግሥት የከተሞችን የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ችግር ለመቅረፍና በዘርፉ የሚነሳውን የህዝብ ጥያቄ ለመመለስ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ የተናገሩት ደግሞ የጨፌ ኦሮሚያ አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ሰዓዳ አብዱረህማን ናቸው። የክልሉ መንግስት የንፁህ መጠጥ ውሃ ተደራሽነትን ጨምሮ በገጠርና በከተሞች የህዝቡን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ለመመለስና መልካም አስተዳደርን ለማረጋገጥ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። የመጠጥ ውሃ ጥያቄው በየጊዜው በጨፌው ላይ የሚነሳ መሆኑን የጠቀሱት አፈ ጉባኤዋ፣ የሞጆ-አዳማ ፕሮጀክት ዛሬ ተመርቆ አገልግሎት መጀመሩ የህዝቡን የዘመናት ጥያቄ ከመሰረቱ የመለሰ ነው ብለዋል። በተጨማሪም ከተሞች በውሃ አስተዳደርና አጠቃቀም ራሳቸውን እንዲችሉ የህግ ማዕቀፎችና አሰራሮች መዘርጋታቸውን ጠቅሰው፤ የአዳማ ከተማ አስተዳደር በቴክኖሎጂ የታገዘ ዲጂታል አሰራር ተግባራዊ በማድረጉ የፋይናንስ አቅም መፍጠር ተችሏል ብለዋል። ይህም በጥገና፣ በእድሳትና በማስፋፊያ ስራ ራሳቸውን እንዲችሉ ያደርጋቸዋል ነው ያሉት። የኦሮሚያ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ሃላፊ ኢንጂነር ሚሊዮን በቀለ እንደተናገሩት፣ በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 2 ሺህ 233 የውኃ ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት በመብቃታቸው 2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ህዝብ የንፁህ መጠጥ ውሃ ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል። ዛሬ የተመረቀው ፕሮጀክትም 15 ጥልቅ የውሃ ጉድጓዶች፣ 250 ኪሎ ሜትር የመስመር ዝርጋታ እና በቀን 77 ሺህ ሜትር ኪዩብ ንጹህ ውኃ ማቅረብ የሚያስችል አቅም ያለው መሆኑን ተናግረዋል። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ፣ የሞጆ-አዳማ የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክት መመረቅ የከተማዋን የዘመናት የመልካም አስተዳደር ጥያቄ የመለሰና ቅሬታዎችን የፈታ ነው ብለዋል። "ፕሮጀክቱ ረጅም ጊዜን የወሰደና ብዙ ውስብስብ ችግሮችን ያለፈ ቢሆንም፣ ዛሬ ትልቁ ህልማችን እውን ሆኗል፤ የከተማዋን ህዝብ የመጠጥ ውሃ ጥያቄ ለመፍታት ያስቀመጥነውን ግብም አሳክተናል" ሲሉም ገልጸዋል። ከንቲባው አክለውም፣ ይህ ስኬት አዳማን የኢንቨስትመንትና የኢንዱስትሪ ማዕከል ለማድረግ ለተያዘው እቅድ ትልቅ አቅምን እንደሚፈጥር ተናግረዋል።
በክልሉ በበጀት ዓመቱ ከ26 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰብስቧል
Jul 7, 2026 116
ቡታጅራ፤ ሰኔ 30/2018 (ኢዜአ):-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በበጀት ዓመቱ ከ26 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ሃላፊ ቀመሪያ ረሻድ የቢሮውን የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና የ2019 በጀት ዓመት የትኩረት አቅጣጫን በማስመልከት ዛሬ ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥተዋል። በክልሉ ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ በተሰራው ሥራ ውጤት መገኘቱንና ይህንንም አጠናክሮ ለማስቀጠል እንደሚሰራ ገልጸዋል። በ2018 በጀት ዓመት ከመደበኛና ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ከ26 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ መቻሉንም አስታውቀዋል። የተሰበሰበው ገቢ ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ9 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል። በቀጣይም የግብር አሰባሰብ ሥራውን ለማሳካት የግብር ህጉን የማስከበርና ለግብር ከፋዩ ማህበረሰብ ግንዛቤ የመፍጠር ስራዎች በተከታታይነት እንደሚሰሩ አንስተዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብር አሰባሰብ ሂደትንና ቅንጅታዊ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስረድተዋል። በዚህም ክልሉ በ2019 በጀት ዓመት ከ33 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ከመደበኛና ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ለመሰብሰብ መታቀዱን ያነሱት ሃላፊዋ፣ ግብር ከፋዩ ማህበረሰብ ከሐምሌ 1 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ግብሩን በታማኝነት በመክፈል ሃላፊነቱን እንዲወጣም አስገንዝበዋል። በክልሉ የሚገኙ ከ115 ሺህ 790 በላይ የደረጃ የ "ሀ" እና "ለ" ግብር ከፋዮች ግብራቸውን በወቅቱ በመክፈል ለክልሉ ልማት መጠናከር የሚያደርጉትን አስተዋጽኦ እንዲያጠናክሩም ጠይቀዋል። የገቢ አሰባሳብ ስርዓቱን በማዘመን ቀልጣፋና ፈጣን የገቢ አሰራርን ተግባራዊ መደረጉን ያነሱት ሃላፊዋ፣ ግብር ከፋዮችም የጊዜና ጉልበት ብክነትን በሚታደጉ የቴክኖሎጂ አማራጮች ተጠቅመው ግብራቸውን በወቅቱ እንዲከፍሉ አስገንዝበዋል።
ኢትዮጵያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ጀምራ የምታጠናቅቅ ሀገር ሆናለች
Jul 7, 2026 159
አዲስ አበባ፤ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን ጀምራ የምታጠናቅቅ ሀገር ሆናለች ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለፁ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በፕሮጀክት ግንባታ ዙሪያ ማብራሪያቸው፤ መንግስት የጀመራቸው አጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እርምጃዎች ተከታታይ ዕድገት ማስገኘታቸውን አስታውቀዋል። በማሻሻያው ድጋፍ በዚህ ዓመት ብቻ በርካታ ግዙፍ ብሔራዊ ፕሮጀክቶች ተገንብተው መጠናቀቃቸውን አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ተጠናቆ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ጠቅሰው፤ ሰባት የሀገር ውስጥ ኤርፖርቶች ተገንብተው ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን እና ሌሎችም በርካታ የልማት ፕሮጀክቶች በተሳካ ሁኔታ ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን አስረድተዋል። ለአብነትም በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ ከ1 ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ የአስፓልት መንገድ መገንባቱ ጠቅሰዋል። መንግሥት ለረጅም ዓመታት ሳይጠናቀቁ የተጓተቱ ፕሮጀክቶችን በማጠናቀቅ ረገድ በልዩ ትኩረትና ክትትል እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም የተጀመሩትን ፕሮጀክቶች ከዳር የማድረስና አዳዲሶቹን በሂደት የመተግበር ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልፀው አቅም በፈቀደ መጠን የሕዝቡን የዕለት ተዕለት ኑሮ ለማሻሻል የሚያስችሉ ሁለንተናዊ የልማት ሥራዎች በትጋት እንደሚከናወኑ አረጋግጠዋል።
ኢትዮጵያ በአለም ሶስተኛዋ ቡና ላኪ ሀገር ሆናለች-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 7, 2026 268
አዲስ አበባ፤ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ለቡና ልማት የተሰጠው ትኩረት ኢትዮጵያን በአለም ሶስተኛዋ ቡና ላኪ ሀገር እንድትሆን ማስቻሉን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማብራሪያቸው፥ ሀገራዊ የሪፎርም ስራው ለውጭ ምንዛሬ ግኝት ስኬቶች ከፍተኛ አስተዋጽዎ ማበርከቱን ተናግረዋል። በዚህም በዘንድሮው አመት የኢትዮጵያ ከሸቀጦች ኤክስፖርት 11 ቢሊዮን ዶላር በላይ መሆኑን ገልጸው፥ከቡና ኤክስፖርት ብቻ በአመቱ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ተገኝቷል ብለዋል። ኢትዮጵያ የኮፊ አረቢካ መገኛ እንደመሆኗ በየትኛውም ዘመን ቡና ወደ ውጭ ስትልክ ቆይታለች ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥በእነዚህ አመታት ግን ይህ ነው የሚባል ገቢ ማግኘት አልቻለኝም። በዚህም ሀገሪቱ ባለፉት 17 አመታት ቡናን ወደ ውጭ በመላክ ያገኘችው ገቢ 3 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር መሆኑን ገልጸዋል። መንግስት ለቡና ልማት በሰጠው ከፍተኛ ትኩረት ግን በዘንድሮው አመት ብቻ 3 ነጥብ 1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማሳካት መቻሉን ጠቁመዋል። አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለቡና ኤክስፖርት እድገት ስኬት አስተዋጽዎ ማበርከቱን ገልጸው፤ በቡና ልማት ላይ የመጣውን ለውጥ በተጨባጭ የሚያሳይ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አክለውም፥ቡናን ካልተከልን፤ካልተንከባከብን፤ካልለቀምን፤ ካላጠብን፤ካላሸግን እና ካላጓጓዝን ይህ ውጤት ሊመጣ አይችልም ብለዋል። የኢትዮጵያን የሀገር ውስጥ የቡና ፍጆታ ከመቻል አልፈን ለውጭ ገበያ በማቅረብ የመጣው ለውጥ የሀገራዊ የሪፎርሙ ስኬት መገለጫም ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በቡና ልማት እና ኤክስፖርት ላይ ያሳየችው እድገት በአሁኑ ሰዓት ከብራዚል እና ኮሎምቢያ ቀጥላ በአለም 3ተኛ ደረጃ እንድትይዝ አድርጓታል ሲሉ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያን የምርታማነት አቅም ይበልጥ በማሳደግ የኑሮ ውድነት ጫናን ለመቀነስ በትኩረት ይሠራል
Jul 7, 2026 194
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የምርታማነት አቅም ይበልጥ በማሳደግ እና የተለያዩ እርምጃዎችን በመውሰድ የኑሮ ውድነት ጫናን ለመቀነስ በትኩረት እንደሚሰራ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማብራሪያቸው እንደገለጹት፤ መንግሥት የዋጋ ንረትን ለማረጋጋት በርካታ እርምጃዎችን እየወሰደ ይገኛል። ከተወሰዱ ቀዳሚ እርምጃዎች መካከል የሸማቾችን አማራጭ ማሳደግ አንዱ ሲሆን፣ በዚህም የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችን ተደራሽነት ከ2000 በላይ ማድረስ መቻሉን አስታውቀዋል። የኑሮ ውድነቱን ጫና ለማቅለል መንግሥት ከፍተኛ የኢኮኖሚ ድጎማ እያደረገ ይገኛል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በተለይም በነዳጅ ዘርፍ ላይ ይደረግ የነበረው ድጎማ በከፍተኛ ደረጃ መጨመሩን አስታውቀዋል። ቀድሞ የነበረው የነዳጅ ድጎማ በወር 16 ቢሊዮን ብር እንደነበር ጠቁመው፤ በአሁኑ ወቅት 20 ቢሊዮን ብር በመጨመር የድጎማ መጠኑን በወር ወደ 36 ቢሊዮን ብር ማሳደግ መቻሉን ጠቁመዋል። ይህ የሕዝቡን የመግዛት አቅም ለማሳደግ የተመደበ ትልቅ ሀገራዊ አቅም መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ አብራርተዋል። የሀገሪቱ የኢኮኖሚ ዕድገት ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍሎች በየደረጃውና በልፋታቸው ልክ ተጠቃሚ ማድረግ አለበትም ነው ያሉት።
የቤት ልማት የመንግሥት አንኳር ፕሮጀክት ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 7, 2026 163
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2018(ኢዜአ)፦ የቤት ልማት የመንግሥት አንኳር ፕሮጀክት ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ባለፉት የለውጥ ዓመታት 1 ነጥብ 2 ሚሊየን ቤቶች መገንባታቸውንም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስታውቀዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 30ኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ተገኝተው፣ የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት የሥራ አፈጻጸምን በተመለከተ ከምክር ቤቱ አባላት ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም የዜጎችን የመኖሪያ ቤት ጥያቄ ምላሽ መስጠት የሚያስችሉ ሰፊ ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ የቤት ልማት ጉዳይ ከጉባ ብስራቶች መካከል አንዱ መሆኑንና መንግሥት በከፍተኛ ትኩረት እንደሚሠራበት ተናግረዋል። በዚህም መሠረት ባለፉት ሰባት ዓመታት ውስጥ ብቻ 1 ነጥብ 2 ሚሊየን ቤቶች መገንባታቸውን ጠቅሰዋል። በቀጣዮቹ አምስት ዓመታትም 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ቤቶችን በመንግሥት፣ በግል፣ በመንግሥትና በግል አጋርነት እንዲሁም በሌሎች አማራጮች ለመገንባት ዕቅድ ተይዞ ሰፊ እንቅስቃሴ እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህንን ስኬታማ ማድረግ የሚያስችል አዲስ የመኖሪያ ቤት ፖሊሲ በሚኒስትሮች ምክር ቤት መጽደቁን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ግንባታውን በገጠርና በከተማ ለማፋጠን በትጋት እየተሠራ መሆኑን አስረድተዋል። በቴክኖሎጂ የታገዘ የግንባታ ፍጥነትን ለመጨመርም እንደ 3ዲ ያሉ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች ወደ ሥራ እየገቡ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህም በተጨማሪ የግንባታ ግብዓት አቅርቦትን ለማስፋት በርካታ ፋብሪካዎች ወደ ሥራ እየገቡ ሲሆን፣ በዘርፉ የሚሰማሩ የኮንስትራክሽን ሠራተኞችም ተገቢውን ሥልጠና ወስደው ወደ ሥራ እየተሰማሩ መሆኑን ጠቅሰዋል። ቤት በአንድ ጊዜ መግዛት አቅም ለሌላቸው ወገኖችም በኪራይ ወይም ከወርሃዊ ገቢያቸው ላይ እየከፈሉ በረጅም ጊዜ የቤት ባለቤት መሆን የሚችሉበትን የሞርጌጅ ሥርዓት ለመዘርጋት መንግሥት በስፋት እየሠራበት መሆኑን አመላክተዋል። የቤት ልማት የዜጎችን የአኗኗር ዘይቤ የሚያስተካክል፣ ሰፊ የሥራ ዕድል የሚፈጥርና የሀገሪቱን ኢኮኖሚ የሚያነቃቃ መሆኑን በማንሳት፤ መንግሥት ዘርፉን እንደ አንኳር የልማት ፕሮጀክት ወስዶ እየሠራበት እንደሚገኝና ውጤታማነቱም የጋራ ትጋትን የሚፈልግ መሆኑን አስገንዝበዋል።