ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነት ስኬት የተኪ ምርት አቅምን እና የወጪ ንግድ ተወዳዳሪነትን እያሳደገ ነው
Apr 6, 2026 105
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 28/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነት ስኬት የተኪ ምርት አቅምን በማጎልበት የወጪ ንግድ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን እያሳደገ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ገለጸ። በሀገራዊ ለውጡ ማግስት ተቀርፀው ወደ ተግባር የተቀየሩ የብዝሃ-ኢኮኖሚ ስትራቴጂዎች ዛሬ ላይ በግብርና፣ ኢንዱስትሪ፣ ማዕድን፣ ቱሪዝምና ቴክኖሎጂ ዘርፎች ተጨባጭ ውጤት አስገኝተዋል።   የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄና ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያም የኢንዱስትሪ ዘርፍ መዋቅራዊ የድጋፍና ክትትል ሥርዓት በማጎልበት በወጪ ንግድና ተኪ ምርት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን እያረጋገጠ ነው። በኢንዱስትሪ ዘርፍ የተመዘገበው እመርታም በኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ ድርሻ የሚያበረክትበትን ወሳኝ ዕድል በመፍጠር እያገለገለ ይገኛል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ታረቀኝ ቡልልታ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በሀገራዊ ለውጡ ማግስት የኢንዱስትሪ ምርታማነትን የሚያበረታታ አስቻይ የፖሊሲ እርምጃ ተወስዷል።   የኢንዱስትሪ ዘርፍ ስትራቴጂክ የፖሊሲ እረምጃው የአምራቾችን የመሠረተ ልማት፣ የኃይልና የፋይናንስ አቅርቦት ማነቆዎችን በቅንጅታዊ የአሰራር ሥርዓት መፍትሔ መስጠት እንዳስቻለ ተናግረዋል። በተጨማሪም የሀገር ውስጥና የውጭ የኢንዱስትሪ ዘርፍ የኢንቨስትመንት አልሚዎችን ፍሰት በማሳደግ በሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ገንቢ ሚና የሚወጣበትን ወሳኝ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ታምርት ሀገር አቀፍ ንቅናቄም ዝቅተኛ የኢንዱስትሪ የማምረት ታሪክ በመቀየር በዘርፉ ላይ እመርታዊ መነቃቃት መፍጠሩን አንስተዋል። ይህም ኢትዮጵያን የዓለም አቀፍ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት የስበት ማዕከል እንድትሆን እያደረጋት ነው ብለዋል።   የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያም ሌላኛው ለአምራች ኢንዱስትሪ ምርታማነት አቅም የፈጠረ ወሳኝ ዕድል መሆኑን ገልጸዋል። ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ እሳቤውም የኢንዱስትሪ ምርታማነትን በማሳለጥ አስቻይ የተኪና ወጪ ንግድ አቅም እንዲፈጠር ማድረጉን አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የመጀመሪያ ካፒታል ገበያ ሥርዓት ለአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ከፍተኛ ፋይዳ እያበረከተ መሆኑን አብራርተዋል። የካፒታል ገበያም የአምራች ኢንዱስትሪ የፋይናን አቅርቦት ፍላጎትን ምላሽ መስጠት የሚያስችል አማራጭና የረጅም ጊዜ ቁጠባን የሚያበረታታ አስቻይ የአሰራር ምኅዳር እንደፈጠረ አንስተዋል።
ሕገ ወጥ የዋጋ ጭማሪ ተጠያቂነት ያስከትላል- የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር
Apr 6, 2026 178
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 28/2018 (ኢዜአ)፡- ለበዓል በቂ አቅርቦት ስላለ ሕገ ወጥ የዋጋ ጭማሪ ማድረግ ተጠያቂነት የሚያስከትል መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ የተለያዩ ክፍለ ከተሞች የበዓል የግብይት ባዛሮችን ከፍተዋል። ሚኒስትሩ በቂርቆስና አራዳ ክፍለ ከተሞች ባዛሮችን በከፈቱበት ወቅት፤ መሰል የገበያ ትስስር መድረኮች በመላ ሀገሪቱ በሚገኙ ዋና ዋና ከተሞችም እንዲዘጋጁ መደረጉን ተናግረዋል።   በአሁኑ ወቅት በመላ ኢትዮጵያ ከ2 ሺህ 100 በላይ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች ተሰናድተው ሸማቹንና አቅራቢውን በቀጥታ በማገናኘት ላይ እንደሚገኙም አረጋግጠዋል። በባዘሮቹም የግብርናና የኢዱስትሪ ምርቶች ምክንያታዊ በሆነ ዋጋ ለሸማቹ እየቀረቡ መሆኑን አረጋግጠዋል ። በዚህም መሠረት ለምሳሌ ቀይ ሽንኩርት በኪሎ 65 ብር፣ ድንች በኪሎ 40 ብር እንዲሁም አንድ እንቁላል በ14 ብር ሲሸጥ መመልከታቸውን ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በግብርና ምርቶችም ሆነ በሌሎች መሠረታዊ ሸቀጦች ላይ ለዋጋ ጭማሪ ምክንያት የሚሆን ምንም ዓይነት የአቅርቦት እጥረት አለመኖሩንም አስረድተዋል።   ከመካከለኛው ምሥራቅ ወቅታዊ አለመረጋጋት ጋር ተያይዞ የነዳጅ ዋጋ ጭማሪን እንደ ምክንያት በመጠቀም፣ ከነዳጅ ጋር ግንኙነት ባላቸውም ሆነ በሌላቸው ምርቶች ላይ የሚደረግ ሕገ ወጥ የዋጋ ጭማሪ በምንም መልኩ ተቀባይነት እንደሌለውም አሳስበዋል ። ነጋዴው ሕግና ሥርዓትን አክብሮ እንዲንቀሳቀስ ጥሪ ያቀረቡት ሚኒስትሩ፤ ገበያውን ለመረበሽ በሚሞክሩ አካላት ላይ አስፈላጊው ሕጋዊ እርምጃ እንደሚወሰድም አስታውቀዋል ።
በክልሉ ግብርናን በማዘመን በተከናወኑ ተግባራት ምርትና ምርታማነት እያደገ መጥቷል-ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን
Apr 6, 2026 81
አሶሳ፤መጋቢት 28/2018 (ኢዜአ)፦በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርናን በማዘመን በተከናወኑ ተግባራት ምርትና ምርታማነት እያደገ መምጣቱን ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ። 10ኛው ክልላዊ የግብርና ልማት አጋር አካላት የግንኙነት ካውንስል ጉባኤ፣የ2017/18 የመኸር ምርት አፈጻጸም እና የ2018/19 የመኸር ምርት ዕቅድ ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ በአሶሳ ከተማ ተካሂዷል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን እንዳሉት፥ በክልሉ የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን እየተመዘገበ ያለው ለውጥ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባለፈ የኢኮኖሚ አቅሙን እንዲያሳድግ አድርጓል። አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም እየተከናወነ የሚገኘው የግብርና ሥራ ሰፋፊ ማሳዎችን በዘር ከመሸፈን ባለፈ ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጉን ተናግረዋል። በክልሉ በሌማት ትሩፋት፣በአረንጓዴ አሻራ፣በሩዝ፣ በስንዴና በተፋሰስ ልማት እየተከናወኑ የሚገኙ አበረታች ተግባራትን በማጠናከር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደግ እንደሚገባ ገልጸዋል። መንግሥት ለግብርናው ዘርፍ ልዩ ትኩረት በመስጠት ያከናወናቸው የመስኖ ግንባታዎች እና ዘርፉን የሚያሳድጉ ፕሮጀክቶች ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ባበክር ሀሊፋ በበኩላቸው፤ በ2017/18 የመኸር እርሻ 55 ሚሊዮን ኩንታል ምርት መሰብሰቡን አስታውቀዋል። በ2018/2019 የመኸር እርሻ በክልሉ 2 ሚሊዮን ሄክታር መሬትን በማልማት ከ70 ሚሊዮን በላይ ኩንታል ምርት ለማግኘት ዕቅድ መያዙን ኃላፊው ገልጸዋል። በመድረኩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ የዘርፉ አመራሮች እና ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያ ከኳታር ጋር ያላትን ወዳጅነት ይበልጥ ለማሳደግ በቁርጠኝነት ትሰራለች
Apr 6, 2026 221
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 28/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከኳታር ጋር ያላትን ታሪካዊና ስትራቴጂያዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በቁርጠኝነት እንደምትሰራ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ ገለጹ። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ፣ በኢትዮጵያ የኳታር መንግስት አምባሳደር ሰአድ ሙባረክ አል-ናይሚ ጋር ዛሬ በጽህፈት ቤታቸው ተወያይተዋል። ውይይቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ታሪካዊና ስትራቴጂያዊ ግንኙነት ይበልጥ ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነው። ሁለቱ አመራሮች በቆይታቸው በኢንቨስትመንት መስፋፋት እና በጋራ ተጠቃሚነት ላይ በሚሰሩ የልማት ስራዎች ዙሪያ በዝርዝር መክረዋል። በተለይም የኳታሩ ሹራ ካውንስል (Shura Council) ከብልፅግና ፓርቲ እና ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ጋር ያለውን ግንኙነት ማጠናከር በሚችልባቸው መንገዶች ላይ የጋራ መግባባት ላይ ደርሰዋል። አቶ አደም ፋራህ በብልፅግና ፓርቲ መሪነት በኢትዮጵያ እየተከናወኑ የሚገኙ ዘርፈ-ብዙ የልማት ስራዎችንና እየተመዘገቡ ያሉ ስኬቶችን ለአምባሳደሩ አብራርተዋል። በተለይም ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር ልማት፣ የግብርና ምርታማነት እና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሮች የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ ያላቸውን ጉልህ ሚና በዝርዝር አንስተዋል። አምባሳደር ሰአድ ሙባረክ አል-ናይሚ በበኩላቸው በኢትዮጵያ በተለያዩ የልማት ዘርፎች እየተመዘገበ ያለው ውጤት አመርቂ መሆኑን ጠቅሰው፤ በተለይም ሀገሪቱ ተግባራዊ ያደረገችውን የተሟላ የማክሮ-ኢኮኖሚ ማሻሻያ ተከትሎ ተገማች፣ ግልጽና ምቹ የኢንቨስትመንት ከባቢ መፈጠሩን አመልክተዋል። አምባሳደሩ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ተገኝተው ባደረጉት ምልከታ የልማት ስራዎች ማህበረሰቡን ተጠቃሚ እያደረጉ መሆናቸውን መታዘባቸውንም ገልጸዋል። በተጨማሪም አቶ አደም ፋራህ በመጪው ግንቦት ወር የሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊ እንዲሆን ብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ለአምባሳደሩ ገልጸውላቸዋል። ኢትዮጵያ ለሰፊ ኢንቨስትመንትና ሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት ያላትን ቁርጠኝነትም በዚሁ ወቅት አረጋግጠዋል። የኳታር መንግስት በተለያዩ ዘርፎች ለኢትዮጵያ እያደረገ ስላለው ድጋፍ አቶ አደም ፋራህ ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን፤ ኢትዮጵያ ከኳታር ጋር ያላትን ወዳጅነት ይበልጥ በማሳደግ ለሁለቱ ሀገራት ሕዝቦች የጋራ ተጠቃሚነትና ለቀጣናዊ መረጋጋት በቁርጠኝነት መስራቷን እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል።
በምዕራብ ወለጋ ዞን ከ119 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ እየቀረበ ነው
Apr 6, 2026 89
ጊምቢ፣ መጋቢት 28/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ከ119 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ እየቀረበ መሆኑን የዞኑ የኅብረት ሥራ ማህበራት ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ ኅብረት ሥራ ማህበራት ጽሕፈት ቤት የምርት ግብዓትና አቅርቦት ቡድን መሪ አቶ ተሰፋዬ ታሲሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለ2018/19 የምርት ዘመን የመኸር እርሻ 235 ሺህ 572 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለማቅረብ እየተሰራ ይገኛል። እስካሁን ባለው እንቅስቃሴ 119 ሺህ 731 ኩንታል ማዳበሪያ በዞኑ መድረሱን ገልጸው ከደረሰው ውስጥ 18 ሺህ 849 ኩንታል በላይ የሚሆነው ለአርሶ አደሩ ጋር ደርሷል ብለዋል።   ስርጭቱ በዞኑ በሚገኙ አራት ዩኒየኖችና በየደረጃው ባሉ የኅብረት ሥራ ማህበራት አማካኝነት እየተከናወነ መሆኑ ጠቁመዋል። የዘንድሮው የአፈር ማዳበሪያ አቅርቦት በወቅቱ መከናወኑን የገለጹት ቡድን መሪው፤ የአቅርቦት ሂደቱም ካለፉት ጊዜያት በተሻለ ሁኔታ ለአርሶ አደሩ እንዲከፋፈል እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። የላሎ አሳቢ ወረዳ አርሶ አደር ኦላኒ ሀብታሙ፤ ለዘንድሮ የእርሻ ሥራ የሚውል ማዳበሪያ በወቅቱ ለአርሶ አደሩ ለማድረስ እየተደረገ ያለው ጥረት አበረታች መሆኑን ገልጸዋል። ይህም የእርሻ ሥራቸውን በተሟላ ዝግጅት ለማከናወን እንደሚያስችላቸው ተናግረዋል። የጊምቢ ወረዳ አርሶ አደር ቡልቲ ኑሩ በበኩላቸው፤ ማዳበሪያው በኅብረት ሥራ ማህበራት አማካኝነት በጊዜ መሰራጨቱ አሁን ያለውን ዝናብ በመጠቀም የመሬት ዝግጅት ሥራቸውን አስቀድመው እንዲያጠናቅቁና የተሻለ ምርት እንዲያገኙ እንደሚረዳቸው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ኢ- ተገማችና ተለዋዋጭ ሁኔታን ታሳቢ በማድረግ ቀደም ብላ የአፈር ማዳበሪያ ግዥ በመፈጸም ወደ ሀገር ውስጥ ማስገባቷን የግብርና ሚኒስቴር መግለጹ ይታወሳል።  
የለውጡ ዓመታት በሁሉም ዘርፎች ትልልቅ ስኬቶች የተመዘገቡበት ነው- ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)
Apr 6, 2026 123
ቦንጋ፤ መጋቢት 28/2018(ኢዜአ)፦ የለውጡ ዓመታት በሁሉም ዘርፎች ትልልቅ ስኬቶች የተመዘገቡበት ነው ሲሉ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያ ሀገራዊ ለውጥ እውን የሆነበትን 8ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በካፋ ዞን ቦንጋ ከተማ ህዝባዊ የድጋፍ ሰልፍ ተካሂዷል ።   በመርሃ ግብሩ ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድር ኢ/ር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር)፤ መጋቢት 24/2010 ዓ.ም የዴሞክራሲ መሰረት የተቀመጠበትና የመደመር እሳቤ የተበሰረበት ታሪካዊ እለት መሆኑን ገልጸዋል። የለውጡ ሂደት የተለያዩ ፈተናዎች ያጋጠሙት ቢሆንም ችግሮችን ወደ አድል በመቀየር በሁሉም ዘርፎች ትልልቅ ስኬቶች የተመዘገቡበት መሆኑን ተናግረዋል። በብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፎች በመመራት የህዝብን ተጠቃሚነት እውን ማድርግና ምርታማነትን ማሳደግ የተቻለበት መሆኑን ገልጸዋል። በከተሞችም ይሁን በገጠር የቆዩ የህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ደረጃ በደረጃ ምላሽ በመስጠት እድገትና ማንሰራራት እውን እንዲሆን የተሰራበት ስኬታማ የለውጥ አመታት መሆኑን አንስተዋል።   የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ እንዳሻው ከበደ፤ በለውጡ ዓመታት እንደ ሀገር የህዳሴ ግድብን ጨምሮ ሌሎችም ትልልቅ ፕሮጀክቶችን ማጠናቀቅና ሌሎችንም መጀመር መቻሉ በቀጣይ ትልቅ ሀገራዊ ተስፋ የሰነቀ መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም በለውጡ ዓመታት የተመዘገቡ ዘርፈ ብዙ ስኬቶች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ይበልጥ መትጋት ይኖረብናል ብለዋል። የቦንጋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተክለአብ ቡሎ (ዶ/ር)፤ በለውጡ ዓመታት በሁሉም ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶች የተገኙት በህዝቡ ጠንካራ ትብብር መሆኑን አንስተው ተጠናክረው እንዲቀጥሉ እንሰራለን ብለዋል።   በድጋፍ ሰልፉ የከተማዋ ነዋሪዎች፣ በዞኑ ከተለያዩ ወረዳዎች የተውጣጡ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
በአዲስ አበባ ለመጪው የትንሣዔ በዓል የሚሆን በቂ የፍጆታ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ ነው- ንግድ ቢሮ
Apr 6, 2026 155
አዲስ አበባ ፤መጋቢት 28/2018(ኢዜአ)፡- በመዲናዋ ለመጪው የትንሣዔ በዓል የሚሆን በቂ የፍጆታ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ንግድ ቢሮ ኃላፊ ሀቢባ ሲራጅ ገለጹ። የቢሮ ኃላፊዋ የትንሣኤ በዓልን ምክንያት በማድረግ የተከናወኑ የገበያ ማረጋጋት ስራዎችን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል። በዓሉን ምክንያት በማድረግ ተገቢ ያልሆነ የምርቶች የዋጋ ንረት እንዳይፈጠር ለመከላከል በቂ ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል። በተለይ ደግሞ ከተለያዩ ክልሎች ጋር በመተሳሰር የግብርና እና የኢንዱስትሪ የፍጆታ ምርቶች በጥራትና በስፋት ወደ ከተማዋ እንዲገቡ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በከተማዋ በሚገኙ ስድስት የገበያ ማዕከላት፣ በሰንበት ገበያዎች፣ በሸማች ማህበራት እና በንግድ ስራ ድርጅት በቂ ምርት ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ ነው ብለዋል። እንዲሁም በአስራ አንዱም ክፍለ ከተሞች ዛሬ ከሰዓት ጀምሮ ምርቶች ለግብይት የሚቀርቡበት ባዛር እንደሚከፈት ተናግረዋል። የጤፍ፣ የሽንኩርት፣ የዘይት ፣የእርድ እንስሳት እና ሌሎች የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶች በስፋት እየቀረቡ እንደሚገኝም አብራርተዋል። የግብርና እና የኢንዱስትሪ ምርቶችም ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው ህብረተሰቡ ክፍሎችን የመግዛት አቅም ታሳቢ በማድረግ እንዲቀርብ እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል፡፡ በቀጣይም በዓሉን ምክንያት በማድረግ አላስፈላጊ የዋጋ ጭማሪ እንዳይደረግ ጠንካራና ጥብቅ የክትትል እና ቁጥጥር ስራ እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡  
ለመዲናዋ ነዋሪዎች የገባነውን ቃል በተግባር በመፈጸም ተጠቃሚነትን እናረጋግጣለን - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 5, 2026 534
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 27/2018(ኢዜአ)፦ ለአዲስ አበባ ነዋሪዎች የገባነውን ቃል በተግባር በመፈጸም ተጠቃሚነትን እናረጋግጣለን ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የአዲስ ስፖርት ፓርክን ትናንት መጋቢት 26 ቀን 2018 ዓ.ም መርቀው ለህዝብ ክፍት ማድረጋቸው ይታወቃል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአዲስ ስፖርት ፓርክ ግንባታ በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የምስጋና እና የእውቅና አሰጣጥ መርሃ ግብር አካሂዷል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ አዲስ ስፖርት ፓርክ ሁሉንም የስፖርት ዓይነቶች ማዘውተር የሚያስችሉ መሰረተ ልማቶች የተሟሉለትና ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ የሚያደርግ ዘመናዊ ፓርክ ነው። ፓርኩ የኢትዮጵያን ስም በዓለም አደባባይ ያስጠሩ ዝነኛ አትሌቶች በክብር ታስበው እውቅና ያገኙበት ልዩ ስፍራ መሆኑን በመጥቀስ፤ በዘርፉ አዳዲስ ተሰጥኦ ያላቸውን ወጣቶች በማነቃቃት ብቁ ተተኪዎችን ለማፍራት ታስቦ የተገነባ መሆኑንም አብራርተዋል። ይህ ዘመናዊ ፓርክ ከመዲናዋ የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ጋር የተሳሰረ መሆኑን ጠቅሰው፤ በአዲስ ዕሳቤ የተገነባ ትልቅ የልማት ፍሬ መሆኑን ገልጸዋል። አስተዳደሩ የገባውን ቃል በተግባር በመፈጸም ጥራት ያላቸውንና ዜጎችን በላቀ ደረጃ የሚጠቅሙ ፕሮጀክቶችን ለህዝብ ተደራሽ የማድረግ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። ከንቲባዋ ለአዲስ ስፖርት ፓርክ ግንባታ መሳካት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት በከተማ አስተዳደሩ ስም ምስጋና አቅርበዋል። የአዲስ ስፖርት ፓርክ በአምስት ነጥብ ሰባት ሔክታር መሬት ላይ ያረፈ ሲሆን፤ ከመዲናዋ የወንዝ ዳር ልማት ፕሮጀክት ጋር ተሰናስሎ የተገነባ የስፖርት ማዕከል ነው። በአዲስ አበባ ዑራኤል አካባቢ በተገነባው ፓርክም በዓለም የኦሎምፒክ መድረክ የኢትዮጵያን ስምና ዝና ከፍ በማድረግ የወርቅ ሜዳልያ ያስገኙ 15 ጀግና የአትሌቲክስ ፈርጦችን የሚዘክር ሐውልት ቆሟል። በስፖርት ማዕከሉ ለተተኪ ትውልድ በትዕምርትነት የሚያገለግል ዓለም አቀፍ የኦሎምፒክ ደረጃን ያሟሉ ዘመናዊ የመዋኛ ገንዳ፣ የእግር እና የቅርጫት ኳስ፣ የቴኒስና የሩጫ ትራክንና ሜዳዎችን አካትቷል። በተመሳሳይም በአንድ ጊዜ እስከ ሦስት ሺህ ሰዎችን ማስተናገድ የሚችል ሰፊ ፕላዛ እና በአንድ ጊዜ 300 መኪናዎችን ማስተናገድ የሚችል ባለ ሁለት ወለል የምድር ቤት ተሽከርካሪ ማቆሚያም አካቷል። በልማት ምክንያት ለሚነሱ ዜጎች አቅም የሚያጎለብቱ አዳዲስ የንግድ ሱቆችም የፓርኩ ግንባታ አካል ናቸው።  
የግብርናው ዘርፍ እመርታ በቤተሰብ ደረጃ የአርሶና አርብቶ አደሩን ብልፅግና እያረጋገጠ ነው
Apr 5, 2026 137
አዲስ አበባ፤መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፦የግብርናው ዘርፍ እመርታ በቤተሰብ ደረጃ የአርሶና አርብቶ አደሩን ብልፅግና እያረጋገጠ እንደሚገኝ የክልል የግብርና ዘርፍ የሥራ ኃላፊዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ የብዝኅ ኢኮኖሚ የልማት አቅጣጫ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል ታሪካዊ ስኬት እያስመዘገበ ይገኛል። ለአብነትም በበጋ መስኖ ስንዴ፣ በሌማት ትሩፋት፣ በመኸርና በበልግ የሰብል ምርታማነት ወቅቶች የአርሶና አርብቶ አደሩን የኑሮ ደረጃ በማሻሻል ከፍተኛ ዕድገት ተመዝግቧል። ይህም የኢትዮጵያን የተመፅዋችነት የታሪክ ስብራት በማረም ከራስ አልፎ ስንዴን ለውጭ ገበያ ማቅረብ ያስቻለ አቅም ፈጥሯል። የክልል ግብርና ዘርፍ የሥራ ኃላፊዎች ለኢዜአ እንዳሉትም፤ በከተማና ገጠር በግብርና ዘርፍ የተፈጠረው የምርታማነት አቅም የአርሶና አርብቶ አደሩን የኑሮ ደረጃ እያሻሻለ ነው። በሀገራዊ ለውጡ ማግስት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተተገበሩ የግብርና ምርታማነት ተነሳሽነቶችም የምግብ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥ መሰረት መጣላቸውን ገልጸዋል። የአርሶና አርብቶ አደሩ ዘመናዊ የምርታማነት ሥርዓትም የግብርና ሽግግርን በማፋጠን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ የጽሕፈት ቤት ኃላፊ አሕመድ ሃቢብ እንዳሉት፤ ሀገራዊ ለውጡ የግብርና ዘርፉን በማዘመን የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ጉዞ እያፋጠነ ነው።   የብዝኅ ዘርፍ የኢኮኖሚ ልማት አቅጣጫዎችም የግብርና ሽግግርን በማሳለጥ በቤተሰብ ደረጃ የተሟላ ብልፅግናን እያረጋገጡ መሆኑን ገልጸዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ተግባራዊ የተደረጉ የአርሶና አርብቶ አደሩን ግብርና የማዘመን የልማት መርሃ ግብሮችም እመርታዊ ስኬት ማስገኘታቸውን አስረድተዋል። በቀጣይም በሌማት ትሩፋትና በሰብል ምርታማነት የተመዘገቡ ስኬቶችን በማስቀጠል የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ሥራ ለማፋጠን በትኩረት እንደሚሰራ አንስተዋል። በአፋር ክልል የእርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ የእርሻ ዘርፍ ኃላፊ አሕመድ አሚን በበኩላቸው፤ ሀገራዊ ለውጡ የኢትዮጵያን ግብርና ከዝናብ ጥገኝነት ማላቀቅ ያስቻለ ስኬት አስገኝቷል ብለዋል።   የአረንጓዴ አሻራ፣ የሌማት ትሩፋትና የስንዴ ልማት መርሃ ግብሮች የክልሉን ከፊል አርሶና አርብቶ አደር ማህበረሰብ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ምርታማነትን እያሳደገ መሆኑን ገልጸዋል። የኩታ ገጠም ሜካናይዜሽን የእርሻ ልማት መርሃ ግብርም የግብርና ግብዓት አቅርቦት ሰንሰለትን በማሳለጥ ወሳኝ የምርታማነት አቅም እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የአበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ ምርት በዓለም አቀፍ ገበያ ከፍተኛ ዕድገት እያስመዘገበ ነው
Apr 5, 2026 461
አዲስ አበባ፤መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፦ሀገራዊ ለውጡ ለኢትዮጵያ የአበባ፣ አትክልትና ፍራፍሬ ምርታማነት የሰጠው ትኩረት የዘርፉን ዓለም አቀፍ የገበያ ተወዳዳሪነት ማሳደጉን አምራችና ላኪዎች ገለጹ። የሆርቲካልቸር ዘርፍ የዓለም አቀፍ ገበያ የተወዳዳሪነት አቅም ከቡና ቀጥሎ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ገቢ በማስገኘት በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ዕድገት ላይ የድርሻውን እያበረከተ ይገኛል። የአበባ፣የአትክልትና ፍራፍሬ ዘርፍ የተሰማሩ አምራቾች ለኢዜአ እንዳሉት፤በሀገራዊ ለውጡ ማግስት የዘርፉን ምርታማነት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪነትን እያሳደገ ነው። የኢቲ ሃይላንድ ፍሎራ አበባ አምራችና ላኪ ሥራ አስኪያጅ እመቤት ተስፋዬ፤ ለሆርቲካልቸር የተሰጠው ትኩረት የአበባ ምርታቸውን በአውሮፓና አሜሪካ ገበያ የሚያቀርቡበት ወሳኝ ዕድል ፈጥሯል ብለዋል።   የኢትዮጵያ የአበባ ምርት የዓለም አቀፍ የገበያ ተፈላጊነት እያደገ መምጣቱም ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ገቢ እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ከቲንግ ሲንጀንታ ፍላወር ሳይት ማናጀር መስፍን ግርማ በበኩላቸው፥የኢትዮጵያ የአበባ ምርት በተለያዩ ክፍለ አህጉራት ያለው ከፍተኛ ተፈላጊነት የገበያ መዳረሻ ዕድልን አስፍቷል ብለዋል።   በመንግስት በኩል በመሬት አቅርቦትና ተያያዥ መሠረተ ልማት ግንባታ የተሰጠው ትኩረት ምርታማነትን በማሳደግ የገቢ አቅም እያጎለበተ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም የአበባ ምርታማነት አቅምን በማስቀጠል በኢትዮጵያ አየር መንገድ አማካኝነት ምርትን በጥራትና በፍጥነት ለዓለም ገበያ ለማቅረብ እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል። የሬድ ፎክስ ኢትዮጵያ ዱመኖሬንጅ አበባ ላኪ ማናጀር ራሄል ክፍሌ በበኩላቸው፤አውሮፓ፣ አሜሪካና የእስያ ገበያ የኢትዮጵያ የአበባ ምርት ወሳኝ የገበያ መዳረሻዎች ናቸው ብለዋል።   ይህም የውጭ ምንዛሬ ገቢን በማሳደግ የአበባና ሆርቲካልቸር ዘርፍ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር በሀገር ኢኮኖሚ ላይ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ እንዲጎለብት እያስቻለ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ግብርና ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወንዳለ ሃብታሙ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ የኢትዮጵያን የሆርቲካልቸር ዘርፍ ኢንቨስትመንትና ምርታማነት የሚያጎለብት ምቹ ምኅዳር ተፈጥሯል ብለዋል።   በዚህም የኢትዮጵያ ሆርቲካልቸር በዓለም ገበያ ያለው ተፈላጊነት የውጭ ምንዛሬ ገቢን በማሳደግ በኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ላይ የላቀ ሚና እየተጫወተ መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በአበባ፣አትክልትና ፍራፍሬ ወጪ ንግድ የምታስገኘው ስኬት የሥራ ዕድል ፈጠራና መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግርን እያፋጠነ መሆኑን አንሰዋል።
የመልከ መልካሟ ብዙ መልኮች
Apr 5, 2026 4313
በዮሐንስ ደርበው ✍️ የመልከ መልካሟ ብዙ መልኮች ‘በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ’ ከሚለው ብኂል የላቁና ቁጭት የወለዳቸው ኢኒሼቲቮች - የቱሪዝም ፀጋን ከመግለጥ ባለፈ የገቢ መጠንን እንዲሁም የሥራ ዕድልን እያሳደጉ ነው። ምድረ ቀደምቷ ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ እንደመሆኗ ብዙ ናት። ይህን ሁሉም ሀገራት ስለማያገኙት ዕድለኛም ናት፤ የእኛም ስለሆነች መታደል ነው። የተለያየ የኑሮ ዘይቤ፣ ባህል እንዲሁም ሁሉንም የዐየር ፀባይ ዐቅፋለች። ደግሞም ልዩ ልዩ የተፈጥሮ አቀማመጥ በልዩነት የተቸራት። አሥረጂ ማቅረብ ቢያሻ በሀገሪቱ ከፍተኛ ከሆነው ስሜን ተራራዎች እስከ ዝቅተኛው ስፍራ ዳሎል ያለውን የተፈጥሮ ፀጋ መጥቀስ ሁነኛ ምሥክር ነው። ከሀገራዊ ለውጡ አበርክቶዎች የዘርፉ ባለሙያዎች ‘ካሎሪ አልባው መድኃኒት’ ይሉታል የብርቱዎቹ ልጆች ብርታት በቀጣይ ...! ከመጋቢት ሥጦታዎች መካከል - የጉባ ብሥራቶች ✍️ የተፈጥሮ ችሮታ ለኢትዮጵያ ከብዙ ሥጦታዎቿ መካከል ብሔራዊ ፓርኮችን ብቻ ብናነሳ… የኢትዮጵያ የዱር እንስሣት ጥበቃ ባለሥልጣን በጀት መድቦ በቀጥታ በሥሩ 11 ብሔራዊ ፓርኮችን እና ሁለት የዱር እንስሣት መጠለያዎች ያሥተዳድራል። እነሱም፡- 📌 ስሜን ተራራዎች ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ባሌ ተራራዎች ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 አዋሽ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 አብያታ ሻላ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ነጭ ሳር ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ኦሞ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 አልጣሽ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ገራይሌ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ሃላይደጌ ብሔራዊ ፓርክ፤ 📌 ቃፍታ ሽራሮ ብሔራዊ ፓርክ እንዲሁም 👉 ባቢሌ የዝሆኖች መጠለያ እና 👉 ሲንቂሌ የቆርኬዎች መጠለያዎች ናቸው። ብሔራዊ ፓርኮቹና የዱር እንስሣት መጠለያዎቹ የሀገሬው ሀብት ናቸውና፤ እየተንከባከቡ መጠቀም ይገባል። ✍️ መንግሥት ለኢትዮጵያ ቱሪዝም ከላይ የተገለጹትን ብሔራዊ ፓርኮችና ሌሎችንም፤ ከቤት እንስሣት ንክኪ ነጻ በማድረግ፣ ከልቅ ግጦሽ እንዲሁም ከሕገ-ወጥ ዐደን ለመጠበቅ መንግሥት ብዙ ገንዘብ ያወጣል። የሰው ኃይልና የቁሳቁስ ዐቅርቦትንም ያሟላል። ይህም ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረት ይመሠክራል። በሌላ በኩል የላሊበላ አብያተክርስቲያናት፣ ሶፍዑመር ዋሻን እና የፋሲል አብያተ መንግሥትን ጨምሮ በየክልሎች የሚገኙ ቅርሶችን በመጠገንም እንዲሁ እየተጋ ነው። ከአምስቱ የኢኮኖሚ ምሰሶዎቹ አንዱ የቱሪዝም ዘርፍ ማድረጉም ትኩረቱን ያሳያል። በዚህ ሂደት በየአካባቢው ፀጋዎችን ዕየለየ በርካታ መዳረሻዎችንና የጎብኝ ማረፊዎችን አልምቷል፤ እያለማም ነው። እነዚህም በኢኮኖሚው ብሎም በሥራ ዕድል ፈጠራ ከፍ ያለ ሚና እያበረከቱ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት፤ በገበታ ለሸገር፣ በገበታ ለሀገር እና በገበታ ለትውልድ የተሠሩ መዳረሻዎችን ለአብነት ብንጠቅስ፤ ‘በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ’ ከሚለው ብኂል የላቁና ቁጭት የወለዳቸው ኢኒሼቲቮች ናቸው። የቱሪዝም ፀጋን ከመግለጥ ባለፈ የገቢ መጠንን እንዲሁም የሥራ ዕድልን እያሳደጉ ነው። ኢትዮጵያ ዛሬ ነገንም እየሠራች ነውና፤ በቱሪዝሙ ዘርፍ የሚከናወኑ ተግባራት በተለያየ የኢትዮጵያ ክፍሎች መጭውን ትውልድ ባገናዘበ ሁኔታ እየተሳለጡ ነው። በአፍሪካ መዲና በአንድነት እና የወዳጅነት ፓርኮች ጅማሮውን ያደረገው የዘርፉ ልማት፤ ወደ ወንጪ ኢኮቱሪዝም፣ ጎርጎራ፣ ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት፣ የሸበሌ ሪዞርት፣ ሶፍዑመር ዋሻ፣ ባሌ ተራራዎች ብሔራዊ ፓርክ፣ የዝሆኖች ዳና ሎጂ፣ የኒዒን ሌ ፓልም ሎጂ ድረስ ወዘተ… ዘልቋል። እንደቀጠለም ነው። እነዚህም ፀጋን ለይቶ ወደ ሃብት በመቀየር ሂደት በመንግሥት ብርታት የለሙ መዳረሻዎች ናቸው። መንግሥት ነባር መዳረሻዎችን በመጠገንና በማደሥ፤ አዳዲስ መዳረሻ በመገንባት ለኢትዮጵያ ቱሪዝም አልሠሠተም፤ ብዙ እየሠጠ ነው። ✍️ ከቱሪዝም ዘርፍ አንጻር የሕብረተሰቡ ሚና ቱሪዝም በተፈጥሮው ከበርካታ ጉዳዮች ጋር ይተሣሠራል። በእጅጉ ሰላም ይሻል፤ የሰላም ባለቤት ደግሞ ሕዝቡ ነው። ዘርፉ የቅርሶችንና መዳረሻዎችን ልማትና እንክብካቤም ይሻል። ለዘርፉ የሚሰጥ ትኩረት ሀገርንም፤ ሕዝብንም ይጠቅማል፤ ጥቅሙ ከዕለት ጉርስ እስከ ጥሪት ይዘልቃል። በዚህ ሂደት ሕዝቡ በየአካባቢው ያሉ ብሔራዊ ፓርኮችን፣ ቅርሶችን እና የቱሪስት መዳረሻዎችን የኔ ብሎ መጠበቅ ይኖርበታል። ለምሳሌ፡- ብሔራዊ ፓርክ ወይም በመዳረሻ ላይ ጉዳት ቢደርስ በቀጥታ ተጎጂው የአካባቢው ነዋሪ ነው። ምክንያቱም ቱሪስት ካልሄደና ገቢ ካልተገኘ ገቢ ይደርቃልና።
የነዳጅ አቅርቦት ጫናን ለመቋቋም መንግስት ያሳለፈውን ውሳኔ መሰረት በማድረግ ምርትን በፍትሐዊነት እያከፋፈልን ነው
Apr 5, 2026 156
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፦የመካከለኛው ምስራቅ ወቅታዊ ሁኔታን ተከትሎ የነዳጅ አቅርቦት ጫናን ለመቋቋም መንግስት ያሳለፈውን ውሳኔ መሰረት በማድረግ ምርትን በፍትሐዊነት እያከፋፈሉ እንደሚገኝ የነዳጅ ማደያዎች ገለጹ። በነዳጅ አቅርቦት ላይ የተፈጠረውን ችግር ለመቋቋም የተቀመጡ የመፍትሄ አቅጣጫዎችን በአግባቡ እንተገብራለን -አሽከርካሪዎች የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት በአዲስ አበባ የተለያዩ የነዳጅ ማደያዎች ባደረገው ቅኝት፤ ማደያዎቹ የሚራገፈውን ነዳጅ በፍትሐዊነት ለተጠቃሚዎች እያከፋፈሉ እንደሚገኙ ተመልክቷል።   የመካከለኛው ምስራቅ ግጭትን ተከትሎ በርካታ የዓለም ሀገራት በነዳጅ አቅርቦት ላይ የተፈጠረውን መስተጓጎል ለመቋቋም ጥብቅ የቁጠባ መመሪያዎችን በማውጣት ላይ ይገኛሉ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በወቅታዊ ሁኔታው ሳቢያ በነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለት ላይ የተፈጠረውን ችግር ለመቋቋም ዜጎች ነዳጅን በቁጠባ እንዲጠቀሙ ማሳሰባቸው ይታወቃል። ይህንንም ተከትሎ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር የአቅርቦት ሰንሰለቱን በቁጠባና በጥብቅ ቁጥጥር መምራት የሚያስችል የተፅዕኖ መቋቋሚያ ውሳኔዎችን አስተላልፏል። የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትሩ ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)፤ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ ላይ ይፋ እንዳደረጉት፤ በነዳጅ አጠቃቀም ረገድ ለሚከተሉት ዘርፎች ቅድሚያ እንዲሰጥ መመሪያ ተላልፏል፦ በዚህም መሠረት፡-ነዳጅ የሚያጓጉዙ ተሽከርካሪዎች በማደያ የቅድሚያ ቅድሚያ እንዲሰጣቸው፤ ከፍተኛ አምራችና የኤክስፖርት ድርጅቶች በቀጥታ፣ ልዩ ትኩረት የሚሹ የመንግሥትና የግል ፕሮጀክቶች በቀጥታ፣ የገቢና ወጪ ንግድን ጨምሮ መሠረታዊ የፍጆታ ምርቶችን የሚያጓጉዙ ተሽከርካሪዎች ግብርናን የሚያዘምኑ ትራክተሮች፣ የከተማና ሀገር አቀፍ የብዙሃን ትራንስፖርት ተሽከርካሪዎች እንዲሁም በናፍጣ የሚሰሩ ሌሎች ለህብረተሰብ አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች በቅድሚያ እንዲያገኙ የሚያደርግ የቅድሚያ የነዳጅ አጠቃቀም አሠራር የሚተገበር መሆኑን መግለፃቸው ይታወቃል። የገርጂ ኖክ ነዳጅ ማደያ ሥራ አስኪያጅ መልካሙ ሲያልፍ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ማደያው በመንግሥት የወረዱ መመሪያዎችን በአግባቡ በመተግበር ላይ ይገኛል።   በተለይም ቅድሚያ እንዲሰጣቸው ለተወሰነላቸው ድርጅቶች ሕጋዊነታቸውን በማረጋገጥ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ገልጸዋል። በካዛንቺስ የኦላ ነዳጅ ማደያ ሠራተኛ መሰረት ወንድም በበኩላቸው፤ ለኅብረተሰቡና ለሀገር ልማት ወሳኝ ለሆኑ አካላት በወጣው አሠራር መሠረት ምርቱን እያቀረቡ መሆኑን አብራርተዋል።   የሰባራ ባቡር ቶታል ነዳጅ ማደያ ሱፐርቫይዘር ባዬ መኮንን፤ ነዳጅን ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት በፍትሐዊነት እያከፋፈሉ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   ሚኒስቴሩ ኅብረተሰቡ ነዳጅን በቁጠባ እንዲጠቀም፣ የታዳሽ ኃይል አማራጮችን እንዲከተልና የእግር ጉዞ ባህልን እንዲያጎለብት ጥሪ አቅርቧል። በተጨማሪም የሕዝብ ትራንስፖርትን በመጠቀምና በነዳጅ ግብይት ላይ የሚስተዋሉ ሕገ-ወጥ ተግባራትን በማጋለጥ ረገድ ዜጎች ከመንግሥት ጋር ተባብረው እንዲሠሩ ማሳሰቡ ይታወሳል። የማደያዎቹ የሥራ ኃላፊዎችም በመካከለኛው ምስራቅ የተፈጠረው የሰላም መደፍረስ በሀገር ላይ የሚኖረውን አሉታዊ ጫና ለመቀነስ ሁሉም ሰው በኃላፊነት ስሜትና በትዕግሥት ሊንቀሳቀስ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በሐረሪ ክልል ከሀገራዊ ለውጡ በኋላ የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ምርትና ምርታማነት ማሳደግ ተችሏል
Apr 5, 2026 126
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 27/2018 (ኢዜአ)፦በሀረሪ ክልል ከሀገራዊ ለውጡ በኋላ የግብርናውን ዘርፍ በማዘመን ምርትና ምርታማነት ማሳደግ ያስቻሉ ስራዎች መሰራታቸውን የሐረሪ ክልል ኮሙኒኬሽን ጽህፈት ቤት ገለፀ።   የክልሉ መንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሄኖክ ሙሉነህ እንደገለጹት ባለፉት ስምንት የለውጥ አመታት በሐረሪ ክልል በየዘርፉ ተጨባጭ ውጤት ያመጡ ስራዎች ተከናውነዋል ብለዋል። በክልሉ ከለውጡ ወዲህ ለግብርናው ዘርፍ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት በተሰሩ ስራዎች ውጤት ከተመዘገበባቸው ዘርፎች መካከል አንዱ እንዲሆን ማድረግ ተችሏል። አርሶ አደሩን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅና ያሉ ውስን መሬት በዘር እንዲሸፈን ለአርሶ አደሩ ከስልጠና ጀምሮ አስፈላጊ ግብዓቶችን በማቅረብና በመደገፍ ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ ለማስቻል ዘርፈ ብዙ ስራዎች ተከናውነዋል። ሰፋፊ የመስኖ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክቶች በመገንባት አርሶ አደሩ በመስኖ እንዲያለማ የሚያስችል ስራ ተከናውናል። በተለይም በሰብልና በእንስሳት ምርትና ምርታማነትን፣ በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ እንዲሁም በመስኖ ግንባታ ዙሪያ ዘርፈ ብዙ ተግባራት ማከናውን ተችላል።   እንዲሁም በአትክልትና ፍራፍሬዎች እና በሌማት ትሩፋት የተከናወነው ስራም አበረታች ውጤት ተመዝግቧል። አርሶ አደሩ የሚያለማውን የአትክልት እና ፍራፍሬ ልማት ስራዎች በተመጣጣኝ ዋጋ ለከተማው ማህበረሰብ በማቅረብ የዋጋ ንረቱን ከማረጋጋት ባለፈ ለአርሶ አደሩ የገበያ ትስስር እንዲያገኝ አስችሏል። በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃም በተግባር የተገለጡ ውጤታማ ስራዎች ተከናውነዋል።   በክልሉ ከተማና ገጠር ወረዳዎች በሌማት ትሩፋት፣ በእንስሳት ተዋጽኦና በአትክልትና ፍራፍሬ የተከናወኑ ስራዎች ህብረተሰቡ የኑሮ ውድነት ጫናን ለማቃለልና የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝ አስችለዋል።   በገጠር በመስኖ ልማት የተከናወኑ ስራዎችም ምርትና ምርታማነት እንዲጎለብትና የአርሶ አደሩ ምግብ ዋስትና እንዲረጋገጥ በማገዝ ረገድ ተጨባጭ ውጤት አስገኝቷል። በበልግና መኽር እርሻ የዝናብ እጥረትን ተቋቁመው በአጭር ጊዜ ምርት የሚሰጡ የበቆሎና የማሽላ እርሻ ስራ በእጥፍ እንዲያድግና የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማረጋገጥ አስችሏል። በክልሉ በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና እንክብካቤ የተከናወኑ ስራዎችም አርሶ አደሩ የከርሰ ምድር ውሃን በቅርበት እንዲያገኝ በማስቻሉ ከዝናብ ጥገኝነት ተላቆ ምርትና ምርታማነቱ እንዲጎለብት አድርጓል። በቀጣይም የክልሉ መንግስት የግብርናውን ዘርፍ ለማሳደግ እና ምርትና ምርታማነት ለማጎልበት የሚያከናውናቸውን ስራዎች በላቀ ቁርጠኝነት አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ENA
አዲስ ስፖርት ፓርክ የመደመር እሳቤና ተግባር የታየበት ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 4, 2026 770
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦‎ አዲስ ስፖርት ፓርክ የመደመር እሳቤና ተግባር የተገናኙበት ፕሮጀክት መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የአዲስ ስፖርት ፓርክ ዛሬ መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፣ ፓርኩ የኢትዮጵያን ሁሉን አቀፍ ልማት በተግባር የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል። የኢኮኖሚ ልማት ያለ ሰብአዊ ልማት ምልዑ ሊሆን እንደማይችል ጠቁመው፣ የስፖርት መሠረተ ልማት ማስፋፊያዎች የዚሁ የሰው ተኮር ልማት ተግባር ማሳያ መሆናቸውን አመልክተዋል። የመደመር መንግሥት ዋና እሳቤም ሁሉን አቀፍ ልማትን ለዜጎች ተደራሽ ማድረግ መሆኑንና ዛሬ የተመረቀው ፓርክም ይህ እሳቤና ተግባር የተገናኙበት ትልቅ የስፖርት አውድ መሆኑን አስገንዝበዋል።   ፓርኩ ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ የሁሉም ስፖርቶች መሠረተ ልማት እና የአረንጓዴ መዝናኛ ስፍራዎችን አሟልቶ የተገነባ ነው ብለዋል። ይህም ስፍራ ለወጣቶች መወዳደሪያና ለታዳጊዎች መጎልበቻ ከመሆኑ ባለፈ፣ ለሀገራቸው ትልቅ ክብር ያመጡ የስፖርት ፈርጦች ሐውልት የቆመበት የጀግኖች አምባ ሆኖ እንዲያገለግል ተደርጎ መዘጋጀቱን ነው ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያመለከቱት። በተለይም በፓርኩ ውስጥ የጀግኖች ገጽታ ከነጽናታቸውና ከነአርዓያነታቸው፣ እንዲሁም ፊታቸው ላይ ከተጻፈው የሀገር ፍቅር ጋር ተደምሮ በሐውልት መታሰቢያነት መቆሙን አንስተዋል። ሐውልቶቹ ለኢትዮጵያ የሮጡ እግሮችንና ለሀገር የተከፈለ ውድ ዋጋን በሚዘክር መልኩ በክብር ተቀርጸው የተቀመጡ መሆናቸውንም እንዲሁ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የአዲስ ስፖርት ፓርክ መመረቅ መንግሥት ለሕዝብ የገባውን ቃል እያከበረና ኃላፊነቱን እየተወጣ ስለመሆኑ ትልቅ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። ቃል ተግባር እየሆነ አዲስ አበባም እየተቀየረች፣ ኢትዮጵያም ወደ ክብር ማማ እየገሰገሰች ነው ብለዋል በመልዕክታቸው።
ሞተር አልባ የትራንስፖርት አገልግሎት ወቅቱን የዋጀ ነው
Apr 4, 2026 143
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ ሞተር አልባ የትራንስፖርት አማራጭ ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር የሚስማማና ወቅቱን የዋጀ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር ገለጸ። "የብስክሌት መጋራት" የትራንስፖርት አገልግሎት የማስጀመሪያ መርሀ ግብር ዛሬ በአዲስ አበባ የተካሄደ ሲሆን፤ አገልግሎቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ከመስቀል አደባባይ ቦሌ ድረስ መሆኑም ተገልጿል። ብስክሌቶቹ በሞባይል መተግበሪያ አገልግሎት የሚሰጡ መሆናቸው የተገለጸ ሲሆን፤ የጂፒኤስ ሲስተም እንደሚጠቀሙም በመርሀ ግብሩ ላይ ተመላክቷል። የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ሞተር አልባ የትራንስፖርት አገልግሎት ከአየር ንብረት ጋር ተስማሚ የትራንስፖርት አማራጭ መሆኑን ገልጸዋል። "የብስክሌት መጋራት" የትራንስፖርት አገልግሎቱ ወቅቱን የዋጀ ምላሽ መሆኑንም ተናግረዋል። በአዲስ አበባ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ለብስክሌት መጋራት የትራንስፖርት አገልግሎት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቁመው፤ ለሞተር አልባ የትራንስፖርት አገልግሎት ልዩ ትኩረት መሰጠቱን አመልክተዋል። ዛሬ ይፋ የተደረገው የብስክሌት መጋራት የትራንስፖርት አገልግሎት ዘርፈ ብዙ ፋይዳ እንዳለው ገልጸው፤ ሚኒስቴሩ በሞተር አልባ የትራንስፖርት አገልግሎት ለሚሰማሩ አካላት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ሀላፊ ያብባል አዲስ በበኩላቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ የሞተር አልባ የትራንስፖርት አገልግሎትን ለማስፋት በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በኮሪደር ልማቱ ከ240 ኪሎ ሜትር በላይ የብስክሌት መንገድ መሰራቱን ጠቁመው፤ መሰረተ ልማቱንም በአግባቡ መጠቀም የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ መጽደቁንም ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ስድስት የሚሆኑ የብስክሌት ኦፕሬተሮች ቅድመ ምዝገባ በማድረግ የዝግጅት ስራ ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ዘርፉ የትራንስፖርት አገልግሎትን በጉልህ የሚያሻሽል መሆኑን ገልጸው፤ በሁሉም አካባቢዎች ለማስፋፋት በትኩረት እንደሚሰራ ጠቁመዋል። በዘርፉ ለመሰማራት ፍላጎት ላላቸውም አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግ ገልጸዋል። የትራንስፖርት አገልግሎቱ ከመጀመሩ በፊት በተደረገ ሙከራ ከፍተኛ ፍላጎት መኖሩን መገንዘብ መቻሉን ያመለከቱት የአዲስ ቴክኖሎጂ ሶሉሽን ሀላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ስራ አስኪያጅ ሳተና ዋሬ ናቸው። ለአገልግሎቱ የሚውለው መተግበሪያም በራስ አቅም በሀገር ልጆች መልማቱን ጠቁመዋል። አገልግሎቱ የፋይዳ ቁጥር በማስገባት መጠቀም የሚቻል ሲሆን፤ ክፍያውም በዲጂታል መንገድ በሞባይል የሚፈጸም መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም አገልግሎቱን በተለያዩ አካባቢዎች ለማስፋት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ቢሮ በደንብ ቁጥር 183/2017 የብስክሌት መጋራት እና የብስክሌት መስመር አጠቃቀም ደንብ ማጽደቁ ይታወሳል።  
ኢትዮጵያ በሁሉም መስኮች እየተሰራች ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) 
Apr 4, 2026 97
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ ፈተናዎችን ወደ እድል በመቀየር ኢትዮጵያን በሁሉም መስክ የማጽናት እና የመስራት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአዲስ ስፖርት ፓርክ ዛሬ መርቀው ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሀገር ግንባታ ስራ ሁለት መሰረታዊ ምሰሶዎችን መያዝ እንዳለበት ገልጸው፤ ትናንትን በወጉ እና በቅጡ የሚያስታውስ ነገን የሚሰራ መሆን እንዳለበት አመልክተዋል። በአድዋ ሙዚየም የአባቶቻችንን ጀግንነት እና ነጻነታችንን እንደምናስታውሰው ሁሉ ነገን የምንሰራው በልጆቻችን ነው ብለዋል። መንግስት የኢትዮጵያን የትምህርት ጥራት ለማረጋገጥ 35 ሺህ መዋዕለ ህጻናትን ገንብቶ ለአገልግሎት ማብቃቱን ጠቅሰው ዓላማውም የተሻለ ዝግጁነት ያለው ትውልድ መፍጠር መሆኑን ተናግረዋል። የአምስት ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ ግብ ነገን የሚሰራ ትውልድ ላይ ያተኮረ እንደሆነም ነው ያመለከቱት። የሀገር ግንባታ እና የሰው ልማት የሚቆራኘው በአካዳሚክ እውቀት በሚገኝ ብቻ ሳይሆን በማህበራዊ መስተጋብር ጭምር ነው ብለዋል። አዲስ ስፖርት ፓርክ እንደ አበበ ቢቂላ፣ ምሩጽ ይፍጠር፣ ቀነኒሳ በቀለ፣ ደራርቱ ቱሉ እና ጥሩነሽ ዲባባ ያሉበትን ሐውልቶች መያዙን ጠቅሰው፤ አትሌቶቹ ለትውልድ ምሳሌ የሆኑና ኢትዮጵያን በዓለም መድረክ ያስጠሩ መሆናቸውን አንስተዋል። ለአትሌቶቹ ሐውልቱ የቆመላቸው በህይወት እያሉ ማክበር ስለሚገባም ነው ብለዋል። ፓርኩ በሁሉም መስክ ህጻናት እና ታዳጊዎች ስልጠና መስጠት የሚያስችሉ ስፍራዎችን መያዙንና ይህም ትውልዱ ከአትሌቶቹ እንዲማር መልካም አጋጣሚን ይፈጥራል ነው ያሉት። ህጻናቱ አትሌቶቹን መሆን እየተመኙ ተግተው ከሰሩ ኢትዮጵያን በዓለም መድረክ የሚያስጠሩ አትሌቶችን ማግኘት እንደሚቻል ተናግረዋል። ሳንዘራ ማጨድ አይቻልም ፣ መዋዕለ ንዋያ ሳናፈስ ውጤት መጠበቅ ከንቱ ምኞት ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ስመጥር ስፖርተኞችን ለማፍራት እንደ አዲስ ስፖርት ፓርክ አይነት መሰረተ ልማቶች ወሳኝ መሆናቸውን አብራርተዋል። የስፖርት ፓርኩ በተለያዩ ስፖርቶች ደረጃቸውን የጠበቁ መሰረተ ልማቶች መያዙን ጠቅሰው፤ ይህም ለታዳጊዎች ትልቅ እድል መሆኑን ተናግረዋል። ህጻናት ፓርኮች፣ የስፖርት መሰረተ ልማቶች እና ንጹህ ስፍራዎችን እያዩ ካደጉ ሌላ ሀገር መሄድን መመኘት ትተው በሀገር መኩራትና መስራት እያደገ እንደሚሄድ ገልጸዋል። በዚህ ሂደት ውስጥ ኢትዮጵያ እንደምትገነባ ገልጸው፤ በሁሉም መስኮች ትናንት እና ነገን በማስተሳሰር ሀገርን መገንባት ወሳኝ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ አብዛኛው ህዝቧ ወጣት በመሆኑ ተግቶ መስራት እና ራስን በእውቀት ማበልጸግ ከታቸለ ከኢትዮጵያ አልፎ አፍሪካን የመደገፍ ትቅል እድል እንዳለ አንስተዋል። በክህሎት እና ብቃት ሰዎች ተሰርተው የሚያድጉበት መሰረተ ልማት እንደሚያስፈልግ ጠቅሰው፤ አሁን ላይ የሚሰሩ ስራዎች የነገዋን ኢትዮጵያ እና ትውልድ ታሳቢ ያደረጉ መሆናቸውንም አመልክተዋል። የአዲስ ስፖርት ፓርክ የካዛንችስ መለወጥ እና ማበብን የሚያሳይ መሆኑን ገልጸው ፓርኩ ትውልድ የሚሰራበት ቦታ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በሁሉም መስክ እየተሰራች ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፈተናዎችን ወደ እድል በመቀየር ኢትዮጵያን የማጽናት እና የመስራት ተግባር በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ነው ያስረዱት። ኢትዮጵያን በመስራት ሂደት ውስጥ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ታላቋን ኢትዮጵያ ማለም ብቻ ሳይሆን በተግባር እንገነባታለን - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 4, 2026 463
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ ታላቋን ኢትዮጵያ ማለም ብቻ ሳይሆን በተግባር እንገነባታለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት የአዲስ አበባን እድሳት ለማፋጠን እና የዜጎቻችንን ክብር ለመመለስ የገባነውን ቃል አንዱ ማረጋገጫ የሆነውን የአዲስ ስፖርት ፓርክን በይፋ መርቀን ከፍተናል ብለዋል።   በ5 ነጥብ 7 ሄክታር መሬት ላይ ያረፈው ይህ ፕሮጀክት፤ በኦሎምፒክ መድረክ ለሀገራችን የወርቅ ሜዳሊያ ያስገኙ 15 አትሌቶችን የሚዘክሩ የክብር ሐውልቶችን በፓርኩ መሃል በማቆም፣ የጀግኖቻችን ታሪክ ለተተኪ ትውልድ ስፖርተኞች ተምሳሌት ሆኖ እንዲቀጥል ያደርጋል ሲሉም ገልጸዋል። የኦሎምፒክ ደረጃውን የጠበቀ የመዋኛ ገንዳ፣ ደረጃቸውን የጠበቁ የእግር ኳስ፣ የቅርጫት ኳስና የሜዳ ቴኒስ መሰረተ ልማቶች እንዲሁም የ800 ሜትር የሩጫ ትራክን ጨምሮ፤ እያንዳንዱ የዚህ ማዕከል ክፍል የዓለም አቀፍ መስፈርቶችን እንዲያሟላ ተደርጎ መገንባቱንም አመልክተዋል።   የእውነተኛ ልማት ማዕከል ማህበረሰቡ ላይ መሆን አለበት በሚል እምነት፣ ይህ ፕሮጀክት ከላቀ የስፖርት አገልግሎት ባለፈ በልማቱ ምክንያት ለተነሱ የህብረተሰብ ክፍሎች የኢኮኖሚ አቅም የሚሆኑ 105 አዳዲስ የንግድ ሱቆችን እንዲሁም 3 ሺህ ሰዎችን ማስተናገድ የሚችል ሰፊ ፕላዛ መያዙንም ነው የገለጹት። በተጨማሪም በአንዴ 300 መኪናዎችን የሚይዝ ባለ ሁለት ወለል የምድር ቤት መኪና ማቆሚያ ያለውና ከወንዝ ዳርቻ ልማት ጋር የተሳሰረው ይህ ፓርክ፤ ንፁህና ዘመናዊቷ ኢትዮጵያ እውን ለማድረግ የጀመርነውን ቁርጠኝነት ጉልህ ማሳያ እንደሆነም ተናግረዋል። ታላቋን ኢትዮጵያ ማለም ብቻ ሳይሆን በተግባር እንገነባታለን ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።
በክልሉ የገበያ ማእከላት ጥራትና ብዛት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ እያቀረቡ ነው
Apr 4, 2026 130
ባህርዳር፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የተገነቡ የገበያ ማዕከላት ጥራትና ብዛት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ዋጋን በማረጋጋት አበረታች ውጤት እያስመዘገቡ መሆኑን የክልሉ ንግድና ገበያ ልማት ቢሮ አስታወቀ። በባህርዳር ከተማ የገበያ ማዕከል የግብርና ምርቶች በስፋት የቀረቡበት የትንሳኤ ዋዜማ ባዛር ዛሬ ተከፍቷል። የቢሮው ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ አትክልት አሳቤ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የተገነቡ ማዕከላት አምራቹንና ሸማቹን በቀጥታ በማገናኝት ገበያ ለማረጋጋት እያስቻሉ ነው። በክልሉ በ1 ነጥብ 6 ሚሊየን ብር በጀት በስምንት ሪጂዮፖሊታን ከተሞች የተገነቡት የገበያ ማዕከላት የግብርና ምርትን በብዛት፣ በአይነትና በጥራት እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል። የገበያ ማዕከላቱ አምራቹ እና ሸማቹ በቀጥታ ተገናኝተው የሚገበያዩበት በመሆኑ በህገ-ወጥ ደላሎች ይፈጠር የነበረውን የዋጋ ንረት በማስቀረት ለህብረተሰብ እፎይታን የሰጠ ነው ብለዋል። የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ አስሜ ብርሌ በበኩላቸው፤ የገበያ መእከላቱ ዋጋን ለማረጋጋት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ ናቸው ብለዋል። ዛሬ የተጀመረው ባዛርም አምራችና አቅራቢዎች ምርታቸውን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ እንዲሸጡ ከማስቻሉም በላይ ዘላቂ የገበያ ትስስር ለመፍጠር የሚያግዝ መሆኑን አስረድተዋል። የአማራ ክልል ‎የግብርና ምርቶች መዳረሻ ገበያ ማዕከል ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ተዋቸው ወርቁ፤ ባዛሩ የተከፈተበት የባህርዳር ከተማ የገበያ ማዕከል ስራ በጀመረ በ2 ሳምንት ውስጥ ከ19 ሚሊዮን ብር በላይ ግብይት አከናውኗል ብለዋል። ዛሬ በተከፈተው ባዛርም 120 አምራቾችና አከፋፋዮች ምርቶቻቸውን በጥራትና በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ ማቅረባቸውን ነው የገለጹት። ‎‎የባዛሩ አላማም ጥራት ያለውና ደህንነቱ የተረጋገጠ የምግብ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ ህብረተሰቡ የትንሳኤ በዓልን አቅሙ በሚፈቅደው መሰረት እንዲገበያይ የሚያደርግ እንደሆነም ጠቅሰዋል። በባዛሩ ላይ ሽንኩርት፣ ዘይት፣ ዱቄት፣ እንቁላል፣ ጤፍና ሌሎች የምግብ ምርቶች መቅረባቸውን ስራ አስኪያጁ ገልጸዋል። እስከ ትንሳኤ በዓል ዋዜማ በሚቆየው ባዛርም በግብርና ምርቶች መዳረሻ ገበያ ማዕከል፤ በባህርዳር ከተማ ንግድና ገበያ ልማት መምሪያና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በጋራ የተዘጋጀ መሆኑ ተመልክቷል።
ኢትዮጵያ በያዝነው ዓመት መድኃኒት የማምረት አቅሟን ከ50 በመቶ በላይ ታደርሳለች - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 4, 2026 141
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የሀገር ውስጥ መድኃኒት የማምረት አቅሟን፣ በ2018 ዓ.ም ከ50 እስከ 55 በመቶ ለማድረስ ማቀዷን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በኢትዮጵያ እና በአፍሪካ የሳይንስ ሥነ-ምሕዳር ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ዘመናዊ የምርምር ማዕከልን ዛሬ መርቀው ከፍተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በአንድ ሀገር ጉዞ ውስጥ የሚያጋጥሙ ችግሮችንና ፈተናዎችን ወደ መልካም ዕድል መቀየር እጅጉን አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። የኮቪድ-19 ወረርሽኝ በተከሰተበት ወቅት፣ አፍሪካ ለከፍተኛ አደጋ ትጋለጣለች የሚል ግምት በበለጸጉት ሀገራት በኩል የነበረ ቢሆንም፣ ያ ሳይሆን መቅረቱን አመልክተዋል። ይሁን እንጂ ወረርሽኙ በሽታን አስቀድሞ የመከላከል ዝግጁነት ምን ያህል እንደሚያስፈልግ ትልቅ ትምህርት ሰጥቶ ማለፉን ተናግረዋል።   በወቅቱ መንግስት በምግብ፣ በልብስ እና በመድኃኒት ዘርፎች ራስን መቻል አለብን የሚል ግልጽ አቅጣጫ ይዞ ወደ ሥራ መግባቱን አስታውሰዋል። በዚህም በምግቡ ዘርፍ ስንዴን ጨምሮ ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን ጠቅሰው፣ በመድኃኒት በኩል ግን በሚፈለገው ደረጃ ለውጥ አለመታየቱን ጠቁመዋል። በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅት ኢትዮጵያ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ማምረት የምትችለው መድኃኒት ስምንት በመቶ ብቻ እንደነበርም አስታውሰዋል። በቂ የመድኃኒት ምርት ማምረት አለመቻሉ፣ ሻጮች የግዢ መድኃኒት መያዛቸውና የግሉ ዘርፍ በምርት ሂደቱ ላይ ለመሳተፍ እምብዛም ፍላጎት አለማሳየቱ በመንግስት በኩል ትልቅ ቁጭት እንዲፈጠር አድርጓል ብለዋል። በምግብ፣ በልብስና በመድኃኒት ራሱን ያልቻለ ሀገር የተሟላ ሉዓላዊነት እንደሌለው ጠቅሰው፣ ይህንን ከግምት ውስጥ በማስገባት የተከናወኑ ተግባራት ውጤት ማስገኘታቸውን አመልክተዋል።   ኢትዮጵያ ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ማምረት የምትችለው የመድኃኒት ድርሻ ቀደም ሲል ከነበረበት ስምንት በመቶ አሁን ላይ ወደ 44 በመቶ ከፍ ማለቱን ገልጸዋል። በቅርብ ጊዜያት የሚመረቁ ፋብሪካዎችን ታሳቢ በማድረግም በተያዘው ዓመት የማምረት አቅሙ ከ50 እስከ 55 በመቶ እንደሚደርስም አስታውቀዋል። በሚቀጥሉት አምስት ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያ ቢያንስ መድኃኒትና ክትባትን በራሷ አቅም እንድታመርት በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በአንጋፋው የአርማወር ሐንሰን የምርምር ተቋም የተመረቀው ዘመናዊ የምርምር ማዕከል ከፍተኛ ወጪ የወጣበት መሆኑን ጠቁመው፣ ለማዕከሉ ለመድኃኒትና ክትባት ምርት መሠረት የሚጥሉ ዕውቀቶችን መያዙንም አመልክተዋል። በኮቪድ ወቅት የናሙና ምርመራ ወደ ደቡብ አፍሪካ ይላክ እንደነበር ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ አዲሱ የምርምር ማዕከል እንዲህ ያሉ ምርመራዎችን እዚሁ የማከናወን አቅም እንዳለው ገልጸዋል። ማዕከሉ 40 ላቦራቶሪዎችን፣ የላቁ የጂኖሚክስና ባዮኢንፎርማቲክስ ክፍሎችን እንዲሁም የመድኃኒቶችን ጥራት የሚያረጋግጥ የባዮኢኩዊቫለንስ ማዕከልን ያካተተ ሲሆን፤ ለድንገተኛ የጤና አደጋዎች ምላሽ የመስጠት አቅምን በመገንባት ረገድም እንደ ዋልታ የሚያገለግል መሆኑን አመልክተዋል። ምርምርን ወደ ፖሊሲ፣ ፈጠራን ደግሞ ወደ ተግባራዊ መፍትሔ በመቀየር ረገድ ማዕከሉ በመድኃኒት ምርት ራስን ለመቻልና ዘላቂ የጤና ደህንነትን ለማረጋገጥ የሚረዳ ትልቅ እርምጃ መሆኑን ገልጸዋል። በጥረትና በትጋት ከሰራን ሀገርን ማሳደግና ማበልጸግ እንደሚቻል ይህ ማዕከል ትልቅ ማሳያ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
ለልማት የሚለቀቅ የመሬት ይዞታ ላይ የሚታዩ የካሳ ክፍያና ቅሬታ አቀራረብ ችግሮችን ለመፍታት ቅንጅታዊ አሰራር ሊጠናከር ይገባል
Apr 4, 2026 285
አዳማ፤ መጋቢት 26/2018(ኢዜአ)፦ ለልማት የሚለቀቅ የመሬት ይዞታ ላይ የሚታዩ የካሳ ክፍያና ቅሬታ አቀራረብ ችግሮችን ለመፍታት ቅንጅታዊ አሰራር ሊጠናከር እንደሚገባ የፌዴራል ሕግና ፍትሕ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ ለሕዝብ ጥቅም ሲባል መሬት በሚለቀቅበት ወቅት በካሳ፣ በመልሶ ማቋቋምና በቅሬታ አቀራረብ ላይ በማተኮር የዘርፉ ምሁራን በተሳተፉበት የምርምር ሲምፖዚየም በአዳማ ከተማ ተካሂዷል።   የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ደግፌ ቡላ በመድረኩ እንደገለጹት፤ መንግሥት የሀገሪቱን የመሬት አጠቃቀምና አስተዳደር ሥርዓት በገጠርና በከተማ ለማዘመን በትኩረት እየሠራ ይገኛል። ከዚህ ቀደም የነበረው አሰራር በወረቀት ላይ የተመሠረተ በመሆኑ ለሙስና፣ ለሀብት ምዝበራና ለተለያዩ አስተዳደራዊ ችግሮች የተጋለጠ እንደነበር አስታውሰዋል። የመሬት ይዞታ ለልማት በሚለቀቅበት ወቅት የሚታዩ የካሳ ክፍያና የቅሬታ አቀራረብ ችግሮችን ለመፍታት፣ የፍትሕና ባለድርሻ አካላት የጋራ ግንዛቤ መያዝ እንዳለባቸው ጠቁመዋል። አምባሳደሩ አክለውም ዜጎች ለይዞታቸው ሕጋዊ ዋስትና እንዲያገኙ የዲጂታል ይዞታ ማረጋገጫ (ካዳስተር) ሥርዓት እየተዘረጋ መሆኑን፣ ፍትሐዊ የካሳ አከፋፈል እንዲኖር የሕግ ማዕቀፎች ማሻሻያ ተደርጎ ወደ ተግባር መገባቱን በበጎ የሚታይ መሆኑን አንስተዋል። ዘመናዊ አሰራሩ የይገባኛል ጥያቄዎችንና ግጭቶችን ከመቀነሱ ባለፈ በፍትሕ ሥርዓቱ ላይ የሚታየውን የክርክር መጨናነቅ ማቃለሉን ገልጸዋል። ሕጎችንና አሰራሮችን ማዘመን ብቻውን በቂ አለመሆኑን ጠቅሰው፤ የሕጎቹን ተፈጻሚነትና ውጤታማነት በምርምር በመደገፍ የመፍትሔ ሐሳቦችን ማቅረብ ይገባል ብለዋል። የሪፎርሙን ውጤታማነት ለመገምገም የሕግ ምሁራንና ባለሙያዎች በቅንጅት ሊሠሩ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም