ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የጣና ሐይቅ ተቀድቶ የማያልቅ የልማት ምንጭ፤ የማይደበዝዝ የውበት ጮራ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 3, 2026 142
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018(ኢዜአ)፦ የጣና ሐይቅ ተቀድቶ የማያልቅ የልማት ምንጭ፤ የማይደበዝዝ የውበት ጮራ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው እንዳስታወቁት ለባሕር ዳርና ለአካባቢው ዘርፈ ብዙ ትሩፋት ይዞ የመጣውን ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ዛሬ መርቀን ለአገልግሎት ከፍተናል። ዳርቻ የለሽ የተፈጥሮ ውበት ከሰው ልጆች ትጋት ጋር ሲደመር ምን ውጤት እንደሚገኝ ባሕር ዳር ማሳያ ናት ሲሉም ተናግረዋል።   ባሕር ዳር በኢትዮጵያ ትልቁ ሐይቅ እና በዓለም ትልቁ ወንዝ የሚገናኙባት ከተማ ናት ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዙሪያዋ ፈጣሪ የሰውን መንፈስ በነፍስም በሥጋም ለማደስ የፈጠረው አካባቢ ነው በወዲያ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት አለ ብለዋል በመልዕክታቸው። ተሻግሮ የጎንደር ፋሲለደስ ደረቱን ነፍቶ ይታያል መነሻ በወዲህ በገበታ ለሀገር ኢኒሼቲቭ ተጠንስሶ በአቶ ካሣሁን(ቢአይካ) የተገነባው የፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ይገኛል፤ በመሐል ዓባይና ጣና ናቸው ሲሉም ገልጸዋል። ዛሬ የመረቅነው የፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ለከተማዋና ለሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ተጨማሪ የውበት እና የልማት ከፍታ ነው ብለዋል። መንግሥት ለቱሪዝም መዳረሻዎች የሰጠው ትኩረት ምን ውጤት እንዳመጣ በገሐድ የሚነበብበት ፕሮጀክት ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአካባቢውን የቱሪዝም መሥመርና ሠንሠለት የሚያጠናክር ማረፊያና መዳረሻም ነው።   ሪዞርቱ ዘመናዊ እና ቅንጡ የእንግዳ ማረፊያዎች፣ የመዝናኛ ሥፍራዎች፣ ሱቆች ፣ አምፊ ቴአትር እና መሰል መሠረተ ልማቶችን አሟልቶ፣ ጣናን ተንተርሶ የተሠራ ሪዞርት ነውም ብለዋለ። በባሕር ዳር ኢንቨስት ለማድረግ ሥራ የጀመሩና መሬት የተረከቡ ኢንቨስተሮች እንደ ፈለገ ግዮን ሥራዎቻቸውን በፍጥነት እንዲፈጽሙ አደራ እንላለን ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።
በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ተመርቆ የተከፈተው ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት…
May 3, 2026 144
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትን መነሻ በማድረግ በገበታ ለሀገር ፕሮጀክት አካል ሆኖ በግል ኢንቨስትመንት በባህር ዳር ከተማ የተገነባውን የፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት በዛሬው ዕለት መርቀው ከፍተዋል፡፡   ስለፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት በጥቂቱ፦ ✅በባህር ዳር ከተማ በጣና ሐይቅ ደቡባዊ ዳርቻ ላይ ተገንብቷል፤ ✅በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "ገበታ ለሀገር" እቅድ መሰረት በሐይቁ ሌላኛው አቅጣጫ ከሚገኘው የጎርጎራ ብርሃን (ጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት) ጋር በመቀናጀት የጣናን የቱሪዝም ቀጣና ለማነቃቃት የታለመ ነው፤ ✅ 4 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር ወጪ ተደርጎበታል፤ ✅ በሁለት ዓመት ከስድስት ወር (30 ወራት) ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ተጠናቆ ለምረቃ በቅቷል፤ ✅በሀገር በቀሉ ባለሀብት በአቶ ካሳሁን ምስጋናው (የቤአኢካ ንግድና ኢንቨስትመንት መሥራች) አማካኝነት በግል ኢንቨስትመንት የተገነባ ነው፤ ✅ሪዞርቱ አዲስ በተቋቋመው ሮዳ ሆስፒታሊቲ ግሩፕ ስር ይተዳደራል፤ ✅ሮዳ ሆስፒታሊቲ ግሩፕ ይህንን አዲስ ሪዞርት እና የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትን በአንድ ላይ በማስተዳደር የቀጣናውን የሆስፒታሊቲ አገልግሎት ይመራል፤ ✅ኢኮ-ሪዞርቱ፦ የተፈጥሮ አካባቢን በጠበቀ መልኩ የተገነባ የቱሪስት መዳረሻ ነው፤ ✅በግል ኢንቨስትመንት ቢገነባም፣ በመንግሥት የገበታ ለሀገር ማዕቀፍ ኢኒሼቲቮች ውስጥ ተካትቶ የተመራና ትኩረት የተሰጠው ፕሮጀክት ነው፤ ✅ሪዞርቱ ለአማራ ክልልም ሆነ ለሀገሪቱ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ አዲስ የገቢና የሥራ ዕድል ምንጭ እንደሚሆንም ይጠበቃል።
በአማራ ክልል ተፈጥሯዊና ታሪካዊ ጸጋዎችን ለዓለም የሚያስተዋውቁ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎች እውን እየሆኑ ነው - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
May 3, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018(ኢዜአ)፦ መንግሥት ለቱሪዝም ዘርፍ በሰጠው ልዩ ትኩረት የአማራ ክልልን ተፈጥሯዊና ታሪካዊ ጸጋዎች ለዓለም የሚያስተዋውቁ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎች ግንባታ እውን እየሆነ ነው ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩመህ​ በገበታ ለሀገር ኢኒሼቲቭ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትን መነሻ በማድረግ በባህር ዳር ከተማ ጣና ዳርቻ በባለሀብቱ ካሳሁን ምስጋናው የተገነባውን ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ዛሬ መርቀው ከፍተዋል።   በመርኃ ግብሩ የአማራ ክልል እና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ አባ ገዳዎች፣ ባለሀብቶችና የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች ተገኝተዋል። በባህር ዳር ከተማ በጣና ሐይቅ ደቡባዊ ዳርቻ ላይ የተገነባው ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "ገበታ ለሀገር" እቅድ መሰረት በሐይቁ ሌላኛው አቅጣጫ ከሚገኘው የጎርጎራ ብርሃን (ጎርጎራ ኢኮ ሪዞርት) ጋር በመቀናጀት የጣናን የቱሪዝም ቀጣና ለማነቃቃት የታለመ ነው። ይሄው በአራት ነጥብ አምስት ቢሊየን ብር ወጪ የተገነባው ሪዞርት፤ ሁለት ዓመት ከስድስት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ግንባታው ተጠናቆ ለምረቃ መብቃቱ ታውቋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት እየተገነቡ የሚገኙት የቱሪዝም መዳረሻዎች የክልሉን ውበት ከመግለጽ ባለፈ፣ እስካሁን በበቂ ሁኔታ ያልታወቁ ጸጋዎችን ይፋ እያደረጉ ይገኛሉ። ቀደም ሲል የተገነባው የጎርጎራ ፕሮጀክት፣ ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት እና ሌሎች ግንባታዎች የክልሉን ውበትና የኢትዮጵያን የብልጽግና ከፍታ የሚያሳዩ ተጨባጭ ማስረጃዎች መሆናቸውንም ገልጸዋል።   አዲሱ ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት የጣና ሐይቅን ደህንነት በጠበቀ መልኩ የተገነባ፣ የጥራትና የምቾት መለኪያ ተደርጎ የሚወሰድ መሆኑን አመልክተዋል። ሪዞርቱ በታላቁ ወንዝ ስም የተሰየመ የጎብኚዎች መዳረሻ መሆኑን አመልክተው፤ ክልሉ ከቱሪዝም ዘርፍ ተገቢውን ጥቅም እንዲያገኝ ያስችላል ብለዋል። ፕሮጀክቱ በመንግሥትና በግለሰቦች በጋራ የመሥራት ባህል የተገኘ ውጤት መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህም አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎች ግንባታ እውን እየሆነ መሆኑንና በቀጣይም መሰል የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። ለትውልድ የሚተርፉና ሀገርን የሚያስከብሩ ሥራዎች መሥራታችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል።
የገበታ ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያውያን በላባችን ሀገር መገንባት እንደምንችል ማሳያ ናቸው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 3, 2026 118
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የገበታ ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያውያን በላባችን ሀገር መገንባት እንደምንችል ማሳያ ናቸው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በገበታ ለሀገር ኢኒሼቲቭ የጎርጎራ ኢኮ ሪዞርትን መነሻ በማድረግ በባህር ዳር ከተማ ጣና ዳርቻ በባለሀብቱ ካሳሁን ምስጋናው የተገነባውን ፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርት ዛሬ መርቀው ከፍተዋል። በመርኃ ግብሩ ላይ የአማራ ክልልና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ አመራሮች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ አባ ገዳዎች፣ ባለሀብቶችና የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች ተገኝተዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፤ የሪዞርቱ መገንባት ለክልሉና ለሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል የቱሪዝም ዘርፍ መጠናከር ተጨማሪ አቅም እንደሆነ ገልጸዋል። በጎርጎራና በፈለገ ግዮን ኢኮ ሪዞርቶች መካከል የሚፈጠረው ትስስር ኢኮኖሚያዊ ፋይዳው የላቀ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ጎብኚዎች ከባህር ዳር ወደ ጎርጎራ፣ ጎንደር፣ ራስ ዳሽን፣ ላሊበላና ትግራይ ክልል የሚያደርጉትን ጉዞ በማቀናጀት የቆይታ ጊዜያቸውን እንዲያራዝሙ ዕድል እንደሚፈጥር አስረድተዋል።   የገበታ ፕሮጀክቶች ዓላማቸው ኢትዮጵያ ያላትን ፀጋና ውበት ገልጣ ለዓለም እንድታሳይ ማድረግ ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህም ግብ አሁን ላይ ፍሬ እያፈራ ነው ብለዋል። አክለውም ኢትዮጵያውያን በደማችን ሀገር መጠበቅ እንደቻልን ሁሉ በላባችንም ሀገር ማልማት እንደምንችል በእነዚህ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች እያሳየን ነው ሲሉ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ባህር ዳር በትልቅ የቱሪዝምና የኢኮኖሚ ልማት ምህዋር ላይ እንደምትገኝ ጠቅሰው፤ የዓባይ አዲሱ ድልድይ በጎንደርና በጎጃም መካከል ያለውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ከማጠናከሩ ባለፈ ራሱን የቻለ የቱሪስት መዳረሻ መሆኑን ገልጸዋል። እየተጠናቀቀ የሚገኘው የባህር ዳር ዓለምአቀፍ ስታዲየም ዓለምአቀፍ ውድድሮችን የማስተናገድ አቅም ባለው ደረጃ መገንባቱን ጠቁመዋል። አዲሱ የአውሮፕላን ማረፊያ ተርሚናል ዓለምአቀፍ በረራዎችንና በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ ለአካባቢው ዕድገት የላቀ መሆኑንም አክለዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገር እና ገበታ ለትውልድ ኢኒሼቲቮች ላይ በንቃት ለተሳተፉ ባለሀብቶች ምስጋና አቅርበዋል። ባህር ዳር ሰላም መሆኗን በመግለጽም፣ ዳያስፖራዎች የወሰዱትን መሬት እንዲያለሙ ጥሪ አቅርበዋል።
የኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ አስደናቂ የሆነ የለውጥ ጉዞ አሳይቷል
May 3, 2026 99
የኢትዮጵያ የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ አስደናቂ የሆነ የለውጥ ጉዞ አሳይቷል። ይህ ጉዞ የሀገሪቱን የኢኮኖሚ መዋቅር ከግብርና ጥገኝነት ወደ ኢንዱስትሪ በማዞር፣ የውጭ ምንዛሬን በማዳን እና የሥራ ዕድልን በመፍጠር ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ‎‎ዘርፉ ከሰነቃቸው ዐበይት ዓላማዎች አንዱ፤ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት በመተካት የንግድ ሚዛኑን ማስተካከል ሲሆን ይህ ጥረት ባለፉት አራት ዓመታት አስደሳች ውጤቶችን አስገኝቷል፦ ‎‎የውጭ ምንዛሬ ገቢ፦ ‎የአምራች ኢንዱስትሪው የወጪ ንግድ በ2014 ከነበረበት 358 ሚሊዮን ዶላር፣ በ2018 በዘጠኝ ወራት ብቻ ወደ 433.8 ሚሊዮን ዶላር ከፍ ብሏል። ይህ ማለት በየዓመቱ ከ5 በመቶ በላይ የሚሆን አማካይ አመታዊ ዕድገት ማስመዝገብ ችሏል። ‎‎የተኪ ምርት ስትራቴጂ፦ ‎መንግሥት 96 ስትራቴጂክ ምርቶችን በመለየት በሀገር ውስጥ እንዲመረቱ በማድረጉ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ማዳን ተችሏል። በዚህም ምርትን በሀገር ውስጥ በመተካት የዳነ የውጭ ምንዛሬ ዕድገት በ2014 በጀት ዓመት ከነበረው 0.343 ቢሊዮን ዶላር፣ በ2018 ዘጠኝ ወራት ውስጥ ወደ 4.85 ቢሊዮን ዶላር ደርሷል። ‎‎የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪ የገበያ ድርሻ፦ ‎በተመሳሳይ የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪዎች በገበያው ላይ ያላቸው ድርሻ በከፍተኛ ደረጃ አድጓል፤ በ2014 ከነበረው የ30 በመቶ ድርሻ አሁን ላይ ወደ 46 በመቶ ማደግ ችሏል። ‎‎ኢንቨስትመንት እና የኢንዱስትሪ መስፋፋት፦ ‎ኢንቨስትመንትን ለመሳብ በተደረጉ የህግ ማሻሻያዎች እና የመሠረተ ልማት የማስፋፋት ስራ፣ ዘርፉ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ባለሃብቶችን ቀልብ መሳብ ችሏል። በተለይም ኢትዮጵያ የብሪክስ (BRICS) አባል በመሆኗ እንዲሁም በሌሎች የዲፕሎማሲ ስኬቶች እና የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያዎች፤ የውጪ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት እንዲስፋፋ አድርገዋል። ‎‎በኢንቨስትመንቱ ስራ፤ ባለፉት አራት ዓመታት ብቻ ከ2,800 በላይ አዳዲስ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንቶች ማሳካት የተቻለ ሲሆን በአማካይ በየዓመቱ ከ700 በላይ ኢንቨስትመንቶች በመሳብ ከፍተኛ ስኬት መመዝገብ ተችሏል። ‎‎የሥራ ዕድል እና ኢንዱስትሪዎች፦ ‎ ከ18,000 በላይ አዳዲስ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች ወደ ሥራ የገቡ ሲሆን፣ ቀደም ሲል ተዘግተው የነበሩ 993 ኢንዱስትሪዎች ወደ ስራ እንዲመለሱ መደረጉ ለኢኮኖሚው እድገት ከፍተኛ አቅም ፈጥሯል። ‎በአጠቃላይ፣ ይህ እንቅስቃሴ የኢትዮጵያ አምራች ኢንዱስትሪ በገበያ መር የተመሠረተ ዕድገትን እየተቀዳጀ መሆኑንና ቀጣይ መዳረሻው የተሻለ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት መንገድ ላይ መሆኑን በግልጽ ያሳያል። ‎#PMOEthiopia #EthiopiaDelivers #MadeInEthiopia
የኢትዮጵያ አምራቾች ከማምረት ባሻገር የአፍሪካ ገበያን መጠቀም የሚያስችል የንግድ ትስስር መፍጠር አለባቸው
May 3, 2026 102
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አምራቾች ከማምረት ባለፈ የአፍሪካን ገበያ መጠቀም የሚያስችል የንግድ ትስስር መፍጠር እንዳለባቸው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 25 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ መርቀው ከፍተዋል። ለአራተኛ ጊዜ "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በተዘጋጀው ኤክስፖ ላይ፤ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ቴዎድሮስ ምኅረት፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበልን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ ባለፉት አራት ዓመታት በውጭ ምንዛሬ ከውጭ ይገቡ የነበሩ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በማምረት ረገድ ከፍተኛ ስኬት ተመዝግቧል። አምራቾችና የኢንዱስትሪ ዘርፍ ተዋንያን የኢኮኖሚ አርበኝነትን ሊላበሱ እንደሚገባ የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በዚህም ሌብነትና ኮንትሮባንድን በመጸየፍ እውነተኛ የኢኮኖሚ አርበኛ መሆን ያስፈልጋል ብለዋል። የኢትዮጵያ አምራቾች በአገር ውስጥ የማምረት ተግባር ላይ ብቻ ተወስነው የሚቆዩበት ጊዜ አብቅቶ፣ አሁን ወደ አፍሪካ ሰፊ ገበያ የሚገቡበት ወቅት ላይ መሆኑንም ነው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) የገለጹት። እስካሁን “አምርቱ” በሚል ማበረታቻ ሲደረግ የነበረው ጥረት አሁን አምራቾች የአህጉሪቱን የንግድ ዕድሎች ለመቀላቀል እንዲወጡና እንዲሰማሩ ጥሪ አስተላልፈዋል። አምራቾች አቅም ካላቸው በግል፣ ካልሆነም በጋራ በመጣመር አሊያም ከመንግሥት ጋር በመቀናጀት ኩባንያዎችን በመመስረት ወደ አፍሪካ አገራት ዘልቆ መግባት አገራዊ ግዴታቸው ሊሆን እንደሚገባም አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በራሷ ትልቅ ገበያ ያላት አገር መሆኗን ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በአፍሪካ ደረጃ ያለውን ሰፊ የንግድ ዕድል ለመጠቀም አምራቾች ከማምረት ባለፈ ገበያውን ለመቆጣጠር መዘጋጀት እንዳለባቸው ተናግረዋል። አንዱ አምራች እዚህ እያመረተ ሌላው ደግሞ በውጭ አገራት እያከፋፈለ የአፍሪካን የንግድ ሰንሰለት መቆጣጠር ለነገ የማይባል የቤት ሥራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህ ትልቅ ራዕይ ከግብ እንዲደርስም መንግሥት ለዘርፉ ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠርና አስፈላጊ የሆኑ ድጋፎችን ለማድረግ የራሱን የቤት ሥራ በአግባቡ እንደሚወጣ አረጋግጠዋል።   በሀገር ውስጥ በማምረት 96 የምርት ዓይነቶችን መተካት እንደሚቻል መለየቱን ጠቁመው፤ እነዚህን የኢንዱስትሪ ባለሀብቶች የምርት ዓይነቶች በማወቅና በአገር ውስጥ በማምረት ከውጭ እንዳይገቡ ማድረግ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። በቅርቡም የኢትዮጵያን ፍላጎት ሙሉ በሙሉ መሸፈን የሚያስችል የሴራሚክ ፋብሪካዎች ለምረቃ እንደሚበቁ አስታውቀው፤በዚህም በማምረት ክብራችንን፣ ነጻነታችንን እና እድገታችንን ማፋጠን እንችላለን ሲሉ ገልፀዋል። ኢትዮጵያ በዚህ ዓመት የ10 ነጥብ 2 በመቶ እድገት እንደምታስመዘግብ ገልጸው፤ በግብርና፣ በማዕድን፣ በኢንዱስትሪ፣ በቱሪዝም እና ከሁሉም በላይ በቴክኖሎጂ ዘርፎች አስደናቂ የሆነ ፈጣን እድገት ላይ መሆኗን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በርካታ ምርቶችን ለሀገር ውስጥ ፍጆታ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ገበያም ማቅረብ እየቻለች መሆኗን ገልጸዋል። ለአብነት በመከላከያ ምርቶች ረገድም ቀደም ሲል ከውጭ ይገቡ የነበሩ በርካታ የምርት ዓይነቶችን በአገር ውስጥ ከመተካት ባሻገር ከስድስት በላይ ለሚሆኑ የአፍሪካ ሀገራት ምርቶችን መሸጥ መጀመሩን ተናግረዋል። በመከላከያ፣በልብስ እና በመድኃኒት ምርቶች ራስን መቻል ብቻ ሳይሆን፤ እነዚህን ማምረት የሚያስችሉ ማሽነሪዎችን ጭምር ማምረትና መሸጥ ስንጀምር ሀገራችን በተሟላ ቁመና ላይ ትገኛለች ሲሉ ገልጸዋል።
የአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ ረገድ ጉልህ ሚና እያበረከተ ይገኛል
May 3, 2026 186
‎አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦የአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ ረገድ ትልቅ ሚና እያበረከተ ይገኛል ሲሉ የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሀሳብ አራተኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ዓለም አቀፍ ኤክስፖ አስጀምረዋል። በኤክስፖ መክፈቻ ሥነ ስነ ሥርዓት ላይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ቴዎድሮስ ምኅረት፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች እና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።   የኢንዱስትሪ ሚኒስትር መላኩ አለበል በወቅቱ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት፤ በመደመር መንግሥት ኢትዮጵያ ያላትን አምራች የሰው ኃይል ተጠቅማ የተለያዩ ምርቶችን በማምረት ረገድ እየታዩ ያሉ ተጨባጭ ውጤቶች፣ ሀገሪቷ ከጀመረችው የብልጽግና ጉዞ ምንም የሚያስቆማት ነገር እንደሌለ ማሳያ ነው። በመደመር እሳቤ ትኩረት ከተሰጣቸው ጉዳዮች መካከል የኢንዱስትሪው ዘርፍ ተጠቃሽ መሆኑን ጠቁመዋል። የመደመር መንግሥት ኢንዱስትሪን የሚመለከተው ለሀገር ከሚኖረው ምጣኔ ሀብታዊ ጠቀሜታ ባሻገር የሀገር ሉዓላዊነትን ከማስጠበቅ፣ ከጥገኝነት ተላቆ ራስን ከመቻል እና ከሀገራዊ ክብር ጋር መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚያዊ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ ረገድ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ነው የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ ያረጋገጡት። ኢትዮጵያን ለማበልጸግ ለአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ የምንሰጠው ትኩረት ጫናዎችን ተቋቁሞ ቀጣይነት ባለው መንገድ የምትበለጽግ ሀገርን መፍጠር እንድንችል ትልቅ ሚና ይጫወታል ሲሉም ገልጸዋል። መንግሥት የኢንዱስትሪው መስክ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ እድገት የሚያበረክተውን ሚና ለማጎልበት ዘርፈ ብዙ ተግባራትን በማከናወን ላይ መሆኑን ተናግረው፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የኢንዱስትሪውን ዘርፍ ምርታማነት ለማሳደግ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በማድረግ፣ የፖሊሲ ማዕቀፎችን በማውጣት፣ ለዘርፉ ተዋናዮች ምቹ የስራ ምኅዳርን በመፍጠር ረገድ በርካታ ስራዎችን አከናውኗል ብለዋል። ከዚህም ባለፈ በመስኩ ላይ ተሰማርተው የሚሰሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች በየደረጃው የሚያጋጥማቸውን ልዩ ልዩ ተግዳሮቶች ለመፍታት የአምራች ኢንዱስትሪ ካውንስል በማቋቋም፣ አምራቾችን በስራቸው ውጤታማ እንዲሆኑ የማገዝ ተግባር በስፋት ሲከናወን መቆየቱንም አንስተዋል። በለውጡ ዓመታት በተሰራውም ስራ የሀገሪቷን የማምረት አቅም ማሳደግ መቻሉን የገለጹት የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ፤ በዚህም ተኪ ምርቶች የማምረት አቅም እንዲያድግና የወጪ ንግድ እንቅስቃሴ እንዲሻሻል አድርጓል ነው ያሉት።   የ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ ማኅበረሰቡ በሀገር ውስጥ ምርት ላይ ያለውን ግንዛቤ በማሳደግ ረገድ ትልቅ ሚና መጫወቱንም አብራርተዋል። የኤክስፖው መዘጋጀት ከሚኖረው ጠቀሜታዎች መካከል የአምራች ኢንዱስትሪዎች ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ያላቸው ትስስር ለማጠናከር፣ የልምድ ልውውጥ ለማጎልበት፣ ዘርፉን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሻገር የሚያስችሉ የምርምር እና የቴክኖሎጂ የእውቀት ሽግግር ለማድረግ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል። በቀጣይም በ"ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ ባለፉት አራት ዓመታት የመጡትን ተጨባጭ ለውጦች ለማስቀጠል፣ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ከፋይናንስና ከመሰረተ ልማት አኳያ ያለባቸውን ማነቆዎች የመፍታት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በተጨማሪም በኢትዮጵያ የገጠር ኢንዱስትሪን ማስፋፋት ተግባር ትኩረት የሚሰጠው ጉዳይ እንደሆነም አመላክተዋል።
በማምረት ክብራችንን እና ነፃነታችንን በማስከበር ዕድገትን ማምጣት ይጠበቅብናል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) 
May 3, 2026 121
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያዊያን በማምረት ክብራችንንና ነፃነታችንን በማስከበር ዕድገትን ማምጣት ይጠበቅብናል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከሚያዝያ 25 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆየውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ መርቀው ከፍተዋል። ለአራተኛ ጊዜ "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በተዘጋጀው ኤክስፖ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር፣ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ቴዎድሮስ ምኅረት፣ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አደም ፋራህን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ማምረት ሉዓላዊነትን ያጎናፅፋል፣ አለማምረት ደግሞ ታሪክን ያጎድፋል ብለዋል። ለአብነትም ኢትዮጵያ ፀጋዎቿን አልምታ ባለመጠቀሟ በዓለም አቀፋዊ ወቅታዊ ሁኔታ ሳቢያ ተግዳሮት ገጥሟት እንደነበር አውስተው፤ በዚህም በሁሉም መስክ ማምረት የተሟላ ሉዓላዊነትን የሚያረጋግጥ ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን ታሳቢ በማድረግ አበክሮ መሥራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። አብዛኛውን ፍላጎቱን በገቢ ምርት ላይ ያደረገ ሀገር ነፃና ሉዓላዊ ነኝ ሊል አይችልም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ አምርታ የተሟላ ሉዓላዊነት እንድትጎናጸፍ በኅብረትና በአንድነት በመሥራት ለልጆቻችን ነፃና የተሟላ ሉዓላዊነት የተጎናጸፈችዋን ኢትዮጵያ ዕውን ማድረግ ይጠበቅብናል ብለዋል። የዛሬ አራት ዓመት የተጀመረው የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄም የኢንዱስትሪ ዘርፍ ምርታማነት በጥራት፣ በደረጃና በዓይነት እያደገ መምጣቱን እንደሚያሳይ ተናግረዋል። ዘንድሮ የኢትዮጵያን የ10 ነጥብ 2 ዕድገት ለማረጋገጥም የኢንዱስትሪና የኢትዮጵያ ታምርት የሚፈጥሩት ጥምረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አንስተዋል።   ከዓመታት በፊት የወጪ ንግድ ሦስት ቢሊዮን ዶላር ለመሻገር ሲንገዳገድ እንደነበር አስታውሰው፤ ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ 10 ቢሊዮን ዶላር በማሳካት ታላቅ ድል እንደሚሆን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ዘርፍም የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ሲጀመር የነበረው የአራት ነጥብ ሰባት ዕድገት አሁን ላይ 10 ነጥብ 7 ዕድገት ማስመዝገቡን አስረድተዋል። ባለፉት አራት ዓመታትም ከውጭ ይገባ የነበረን የ14 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር ወጪ በሀገር ውስጥ መተካት እንደተቻለም አስታውቀዋል። በተለያዩ ምክንያቶች ሥራ አቁመው የቆዩ 993 ኢንዱስትሪዎችም መልሰው ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን አንስተዋል። ባለፉት አራት ዓመታትም 3 ሺህ 680 አዳዲስ ኢንቨስትመንቶች የአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፉን መቀላቀል እንደቻሉ ጠቅሰዋል። በኢንዱስትሪ ዘርፍ በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በተኪ ምርትና በወጪ ንግድ ዕድገት ገንቢ ሚና እየተወጡ ለሚገኙ የዘርፉ ተዋናዮች ምስጋና አቅርበዋል። በቀጣይም ካላመረትን ክብርና ነፃነታችንን መጎናጸፍ አንችልም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የቴክኒክ ኮሚቴ በማዋቀር ለዘርፉ ዕድገት ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። አራተኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖም የአዲስ አበባ ነዋሪዎች፣ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች በመጎብኘት ሊያተርፉበት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አራተኛውን 'ኢትዮጵያ ታምርት' ኤክስፖ 2018 በይፋ መርቀው ከፍተዋል
May 3, 2026 95
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን የአምራች ዘርፍ ለማስፋፋት የሚደረገውን ጥረት የሚያጠናክረውን አራተኛውን 'ኢትዮጵያ ታምርት' ኤክስፖ 2018 ዛሬ በይፋ መርቀው ከፍተዋል። ‎‎ኤክስፖው እስካሁን ያሳያቸው እና የተመዘገቡ ዋና ዋና ስኬቶች፦ ‎- የአምራች ዘርፉ ግብዓት አቅርቦት በዓመት ከ9 ሚሊዮን ወደ 15 ሚሊዮን ቶን አድጓል፤ ‎- ለአዳዲስ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንቶች ከ3.4 ጊጋ ዋት በላይ የኤሌክትሪክ ኃይል ቀርቧል፤ ‎- ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች የሚቀርበው የፋይናንስ አቅርቦት ከ8.1 ቢሊዮን ወደ 50 ቢሊዮን ብር ያደገ ሲሆን ለከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች ደግሞ ከ262 ቢሊዮን ብር በላይ ከፍ ብሏል፤ ‎- ለዘርፉ ከ2.28 ቢሊዮን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ ተመድቧል፤ ‎- የፋብሪካዎች የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ አድጓል፤ ‎- የማምረት አቅምና ዕድገት ከ4.8 በመቶ ወደ 10.7 በመቶ ከፍ ያለ ሲሆን፣ በቀጣይም ተጨማሪ ዕድገት ይጠበቃል፤ ‎- ምርትን በሀገር ውስጥ በመተካት እስከ 4.85 ቢሊዮን ዶላር ማዳን የተቻለ ሲሆን የወጪ ንግድም ከፍተኛ እድገት እያሳየ ይገኛል፤ ‎- ከ2,800 በላይ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ የተቻለ ሲሆን፣ ለ1.4 ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል። ‎ ‎ኤክስፖው ኢንዱስትሪዎችን የሚያስተሳስር፣ ኢንቨስትመንትን የሚስብ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ አምራቾችንና በአሥር ሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችን የሚያገናኝ ቁልፍ ሀገራዊ መድረክ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል። ‎በአጠቃላይ የኤክስፖው መከፈት የአምራች ዘርፉ ለኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ያለውን ፋይዳ በማጉላት የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ሽግግር እያፋጠነ መሆኑን እንደሚያሳይም ተመላክቷል።
‎በዘንድሮው “ኢትዮጵያ ታምርት” ኤክስፖ ላይ የሀገራዊ ርዕያችንን ተጨባጭ ስኬት መመልከት ትልቅ ክብር ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
May 3, 2026 107
‎አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦በዘንድሮው “ኢትዮጵያ ታምርት” ኤክስፖ ላይ የሀገራዊ ርዕያችንን ተጨባጭ ስኬት መመልከት ትልቅ ክብር ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የአራት ዓመታት ተከታታይ ጥረት እና የሚጨበጥ ውጤት! በሚል በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ‎በዘንድሮው “ኢትዮጵያ ታምርት” ኤክስፖ ላይ የሀገራዊ ርዕያችንን ተጨባጭ ስኬት መመልከት ትልቅ ክብር ነው ብለዋል።   በውጤት ተኮር አመራራችን ከዚህ ቀደም ታይቶ በማይታወቅ የኢንዱስትሪ መስፋፋት ተንጸባርቋል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ ይኸውም የአምራች ኢንዱስትሪዎችን አማካይ የማምረት አቅም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ ከፍ በማድረግ፣ ባለፉት አራት አመታት ከ2,800 በላይ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ የተቻለ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ እንዲሁም በ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ በሀገር ውስጥ ተኪ ምርት ከ4.85 ቢሊየን ዶላር በላይ የውጭ ምንዛሬ በማዳን መረጋገጡን አመላክተዋል።   ኤክስፖው ከመላው የሀገሪቱ የተወጣጡ ንቁ አምራቾችን እና ስታርትአፖችን በጨመረ ዐቅም በአንድነት ማሰባሰቡን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‎በጋራ በመሆን ይህንን ጠንካራ መነቃቃት በማስቀጠል፣ ለሚመጣው ትውልድ ጸኑ፣ በኢንዱስትሪ የበለጸገች እና ራሷን የቻለች ኢትዮጵያን እንገነባለን በማለት መልዕክት አስተላልፈዋል።
አዲስ አበባን ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ውጤት እያስገኙ ነው
May 3, 2026 128
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦አዲስ አበባን እንደስሟ ውብና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ውጤት እያስገኙ መሆናቸውን የከተማዋ ቱሪዝም ኮሚሽን አስታወቀ። መንግስት ካለፉት የለውጥ ዓመታት ወዲህ ኢትዮጵያን ተወዳዳሪ የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ ሀብቶችን በመግለጥ፣ በርካታ አዳዲስ የቱሪስት መዳረሻዎችን በማልማትና በነባሮቹ ላይም እሴት የመጨመር ስራዎችን አከናውኗል። የአፍሪካ ህብረት፣ የበርካታ ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ ድርጅቶች እንዲሁም የኤምባሲዎች መቀመጫ የሆነችውን አዲስ አበባን ስሟን የሚመጥን የቱሪዝም መዳረሻ ለማድረግ እና ዘላቂ የቱሪዝም ልማትን ለማረጋገጥ በርካታ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ።   ለውጡን ተከትሎ መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉ የሰጠው ትኩረት እና በተሰሩ የልማት ስራዎች አዲስ አበባ ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን አስችሏታል። ለአብነትም የእንጦጦ፣ አራዳ፣ ወዳጅነት፣ አንድነት ፓርኮች እንዲሁም በከተማዋ መሃልና ዙሪያ ያሉ ተፋሰስ ወንዞችን እና የኮሪደር መሰረተ-ልማቶችን ጨምሮ ሌሎች የአረንጓዴ ልማት ስፍራዎች ይጠቀሳሉ። በዚህም ከተማዋ ያላትን የተፈጥሮ፣ ታሪካዊና ባህላዊ መስህቦች በመጠቀም ረገድ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃንና የአካባቢ ዘላቂነትን ከማረጋገጥ ጋር ተያይዞ ትልልቅ ስራዎች ተሰርተዋል። ይህም አዲስ አበባን ልዩ የኢኮ ቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን፤ ባህልን፣ ታሪክንና ተፈጥሮን አጣምራ የያዘች ልዩ መስህብ አድርጓታል። የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሁንዴ ከበደ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ በለውጡ ዓመታት በተለይም በቱሪዝም ዘርፍ አስደናቂ ተግባራት ተከናውነዋል።   በመዲናዋ በአጭር ጊዜ ውስጥ ጥራትና ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ ግንባታዎች ተከናውነው ስራ መጀመራቸውን ገልጸዋል። በመሆኑም በከተማዋ ያሉ የቱሪዝም መስህብ ስፍራዎችን በማልማት፣ ቅርሶችን በመጠበቅ፣ በማስተዋወቅና የኢኮኖሚ ምንጭ በማድረግ በኩል ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል ሲሉም ተናግረዋል። ከለውጡ ወዲህ በመዲናዋ የተሰሩት የልማት ስራዎች የተለያዩ የቱሪዝም መዳረሻ ቦታዎች እንዲፈጠሩ ማስቻሉን ገልጸው፤ አዲስ አበባን እንደስሟ ውብና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጨባጭ ውጤት አስገኝተዋል። ለውጡን ተከትሎም በኮሪደር ልማት ከተማዋን ለኑሮ ምቹ፣ ፅዱና ማራኪ በማድረግ፤ ስሉጥ የእግረኛ፣ የብስክሌትና የተሽከርካሪ መንገዶችን ጨምሮ አረንጓዴ መናፈሻዎች በመገንባታቸው በዘርፉ ላይ እድገት መመዝገብ መቻሉን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ አዲስ ኢንዱስትሪያዊ ስብዕና እና የስራ ባህል እየገነባ ነው
May 3, 2026 157
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ታምርት ከቴክኒካዊ ብቃት ባሻገር፣ አዲስ ኢንዱስትሪያዊ ስብዕና እና የላቀ የሥራ ባህል በመፍጠር ረገድ ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመረው ኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ፤ 830 ፋብሪካዎችን ዳግም ወደ ስራ በማስገባት፣ 4 ነጥብ 85 ቢሊየን ዶላር ገቢ ምርትን በመተካት እና 433 ሚሊየን ዶላር ከኤክስፖርት በማስገኘት አስደናቂ የኢንዱስትሪ ሽግግር ውጤት ማስመዝገቡንም አመልክቷል። ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ መንግሥት ንቅናቄውን ሲጀምር ግቡ ምርትን ማሳደግና የውጭ ምንዛሬን መታደግ ብቻ እንዳልነበረ አገልግሎቱ ገልጿል። ከኢኮኖሚያዊ ስሌቶች ባሻገር፣ ትልቁና ስትራቴጂካዊው ስኬት የተመዘገበው ኢትዮጵያን የዕውቀትና የክህሎት ምንጭ በሚያደርገው የሰው ሀብት ልማት ላይ መሆኑ ተመላክቷል። ዛሬ ላይ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉ የፋብሪካዎች ስብስብ መሆኑ ቀርቶ፣ የነገዋን ኢትዮጵያ የሚገነቡ ብቁ ባለሙያዎችና መሪዎች የሚፈሩበት ታላቅ የተግባር ትምህርት ቤት መሆን ችሏል። ይህ ሽግግር ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተወዳዳሪነት ከጥሬ ዕቃ ላኪነት ወደ ቴክኖሎጂ ላኪነትና ክህሎት አቅራቢነት ከፍ የሚያደርግ ለነገዋ ኢትዮጵያዊ መሠረት የሚጥል የታሪካችን እጥፋት መሆኑን ነው አገልግሎቱ ያስታወቀው። በታላላቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች፣ በኢንዱስትሪ ፓርኮችና በግዙፍ ፋብሪካዎች ውስጥ የታየው ተጨባጭ ለውጥ የመንግሥትን የፖሊሲ ጥንካሬ በተግባር የሚያረጋግጥ ነው ተብሏል። ከዚህ ቀደም በከፍተኛ ክፍያ በሚመጡ የውጭ ሀገር ዜጎች ብቻ ይተዳደሩ የነበሩ ውስብስብ የቴክኖሎጂ ሲስተሞች፣ ዘመናዊ የምርት መስመሮችና የሶፍትዌር መሠረተ-ልማቶች ዛሬ ላይ ሙሉ በሙሉ በሀገር ውስጥ ወጣት መሐንዲሶችና ቴክኒሻኖች እየተመሩ ይገኛሉ። ይህ ስኬታማ የዕውቀት ሽግግር፣ መንግሥት ጥራት ያለው ፖሊሲ የመቅረጽ ብቻ ሳይሆን ፖሊሲን በተጨባጭ ወደ ተግባር የመለወጥና የማስፈጸም አቅም እንዳለው ትልቅ ማሳያ መሆኑ በመረጃው ላይ ተብራርቷል። በዘርፉ የተሠማሩ ኢትዮጵያውያን ወጣቶችም የተፈጠረላቸውን ምቹ ዐውድ ተጠቅመው ቴክኖሎጂን የመቀበል ብቻ ሳይሆን፣ የመግራትና የማላመድ ብቃታቸውን በተግባር እያሳዩ ይገኛሉ። በዚህም ኢትዮጵያ ለዘመናት የነበረባትን የቴክኖሎጂ ጥገኝነት በፈጠራ አቅማቸው እያስቀሩና አዳዲስ የሥራ ባሕልና የታሪክ ምዕራፍ እየጻፉ መሆኑን አገልግሎቱ ገልጿል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከቴክኒካዊ ብቃት ባሻገር፣ አዲስ ኢንዱስትሪያዊ ሰብዕና እና የሥራ ባህል እየገነባ ይገኛል። በዘርፉ የተሰማሩ ዜጎች ዓለም አቀፍ የጥራት ቁጥጥር ስታንዳርዶችን፣ ጥብቅ የጊዜ አጠቃቀምንና ስልታዊ የአመራር ክህሎትን በመላበስ ላይ ናቸው። ከታችኛው የሥራ እርከን ተነስተው በዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ውስጥ እስከ ከፍተኛ የውሳኔ ሰጪነት ደረጃ የደረሱ ወጣቶች፣ ኢትዮጵያ ለዓለም ገበያ የምታቀርበው "ምርጥ ምርት" የሰው ሀብቷ መሆኑን እያስመሰከሩ መሆኑ ተጠቁሟል። መንግሥት የኢንዱስትሪ ሽግግሩን ትክክለኛ ፍሬ የሚለካው በወጪ ንግድ ስሌቶች ብቻ ሳይሆን በቴክኖሎጂ የደረጀና በዕውቀት የበለጸገ አምራች ዜጋ መፈጠሩ መሆኑን አገልግሎቱ አስታውቋል። በመሆኑም ይህን የክህሎት አብዮት ይበልጥ በማፋጠንና ዘርፉን የቴክኖሎጂ ምንጭ በማድረግ፣ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎች በቁርጠኝነት እንደሚቀጥሉም ገልጿል።
ተፈጥሯዊና የባህል ሀብቶችን ለቱሪዝም ልማት ለማዋል የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው 
May 2, 2026 224
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ የተፈጥሯዊና የባህል ሀብቶችን ለቱሪዝም ልማት ለማዋል የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ተመላከተ። "በኢትዮጵያ ዘመናዊ ቱሪዝም ልማት ውስጥ ፈጠራና ዘላቂነት" በሚል መሪ ሀሳብ ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮጵያ ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 15ኛው ሀገር አቀፍ የምርምር ኮንፍረንስ ተካሂዷል።   በኮንፈረንሱ የዩኒቨርሲቲው ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ችሮታው አየለ (ዶ/ር) እንዳሉት ዩኒቨርሲቲው በቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ የትምህርት መስክ ተማሪዎችን ከማሰልጠን ባለፈ የጥናትና ምርምር ሥራዎችን በማድረግ ዘርፉ ለሀገር እድገት ያለውን ፋይዳ ለማሳደግ የበኩሉን እየተወጣ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ በተጀመረው ገበታ ለሀገርና ገበታ ለትወልድ መርሀ ግብር በርካታ የመስህብ ስፍራዎች መልማታቸውን የማልማት ሥራ መሰራቱን ለማሳያነት ጠቅሰዋል። በቀጣይም ተፈጥሯዊና የባህል ሀብቶችን ለቱሪዝም ልማት ለማዋል የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸውም አክለዋል።   የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጌታቸው ነጋሽ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የሆቴልና ቱሪዝም ዘርፉ በዓለማችን እጅግ ከፍተኛ ትኩረት እያገኙ ከመጡ የሥራ መስኮች አንዱ ነው። በአትዮጵያ በርካታ የመስህብ ሥፍራዎች ቢኖሩም አልምቶ ከመጠቀም እንጻር ተግዳሮቶች እንደነበሩ አስታውሰው፣ በለውጡ መንግስት የመዳረሻ ስፍራዎችን በማስፋፋት ኢትዮጵያ ተመራጭ የቱሪዝም መዳረሻ እንድትሆን ተሰርቷል ብለዋል።   የኢትዮጵያ ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተርና በኮንፈረንሱ ጥናት ያቀረቡት ይታሰብ ስዩም፣ በዘመናዊ የቱሪዝም ልማት ውስጥ አዳዲስ ፈጠራና ዘላቂነትን መሰረት ያደረገ የማልማትና ማስተዋወቅ ሥራ መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን አንስተዋል። የቱሪዝም መሰረተ ልማትን ከቴክኖሎጂ ጋር የማስተሳሰርና አገልግሎቱን ማዘመን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ፋይዳውን ከማሳደግ ባለፈ ሀብቱ ለትውልድ እንዲተላለፍ ያግዛል ብለዋል።   በስነምህዳር ቱሪዝም (ኢኮ ቱሪዝም) ዙሪያ የምርምር ሥራቸውን ያቀረቡት በቦረና ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ ጸለፎ ጫካ፣ በሀገራችን ቱሪዝምን ከስነምህዳር ጋር በማስተሳሰር እየተሰራ ያለው ሥራ በርካታ ጎብኚዎችን እየሳበ መሆኑን ገልጸዋል። የመዳረሻ ልማት ሥራዎች የአካባቢውን ማህበረሰብ፣ ባህል፣ አኗኗር እና አረንጓዴ አሻራን ያስተሳሰረ በመሆኑ ትልቅ ፋይዳ እንዳለውና በከተሞች የተጀመረውን የቱሪዝም መሰረተ ልማት ተደራሽነት ወደ ሌሎች ማስፋፋት እንደሚገባ ጠቁመዋል። በመድረኩ ከቱሪዝም ጋር የተያያዙ ጥናታዊ የምርምር ሥራዎች የቀረቡ ሲሆን ከሀዋሳና ሌሎች ዩኒቨርሲቲዎች የተወከሉ ምሁራን፣ የቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት መምህራንና በቱሪዝም ዘርፍ የተሰማሩ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
በዞኑ በመኸር እርሻ በዘር ከሚሸፈነው መሬት ከግማሽ በላይ የሚሆነው በኩታ ገጠም የሚለማ ነው
May 2, 2026 136
ደሴ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን በመጪው የመኸር እርሻ በዘር ከሚሸፈነው 432 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ ከግማሽ በላይ የሚሆነው በኩታ ገጠም እንደሚለማ የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። አስተዳደሩ የ2018/19 መኸር ምርት ዘመን የሰብል ልማት ንቅናቄ መድረክ ዛሬ በደሴ ከተማ አካሂዷል።   የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪ አሊ ይማም በመድረኩ እንደገለጹት፣ የመኸር እርሻ በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት የተያዘውን ግብ የሚሳካበት ነው። በመኸር እርሻ ከሚለማው 432 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ከ249 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በኩታገጠም እንደሚለማ ገልጸዋል። በአጠቃላይ ለመሰብሰብ ከታቀደው ከ16 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ከ10 ነጥብ 6 ሚሊየን ኩንታል በላይ የሚሆነው በኩታ ገጠም ከሚለማው ሰብል እንደሚሰበሰብ አስታውቀዋል። በልማቱ ምርታማነትን ለማሳደግ የግብርና ቴክኖሎጂና አዳዲስ አሰራሮችን እንዲሁም ግብዓትን በአግባቡ መጠቀም ላይ አቅጣጫ ተቀምጦ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።   የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አህመድ ጋሎ በበኩላቸው በመኸሩ የታቀደውን ምርት ለማግኘት ለአርሶ አደሩ የተጠናከረ ድጋፍና ክትትል ይደረጋል ብለዋል። በተለይም የሜካናይዜሽን እርሻ ላይ በማተኮርና የተሻሻሉ የግብርና አሰራርና ቴክኖሎጂዎችን በመተግበር የምርት ዕድገትን ለማረጋገጥ ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል።
በክልሉ የሚገኙ የልማት ድርጅቶች ልማትን ለማስቀጠል ያላቸውን እቅም እንዲያጠናክሩ እየተሰራ ነው
May 2, 2026 129
ባህርዳር፤ ሚያዚያ 24/2018 (ኢዜአ)፦ የልማት ድርጅቶች በክልሉ እድገት ውስጥ ያላቸውን አበርክቶ እንዲያጠናክሩ እየተሰራ መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአማራ ክልል ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) ገለጹ። በአማራ ልማት ማህበር (አልማ) የተቋቋመው አልማኮን የህንጻ ኮንስትራክሽን ተቋራጭ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት ዛሬ ማምሻውን አዲስ ብራንዱ ይፋ ተደርጓል። የአማራ ክልል ማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት፤ በክልሉ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ልማትን ለማሳደግ የአጋር አካላት ተሳትፎ የጎላ ሚና እያበረከተ ነው። በመሰረተ ልማት ግንባታና ማህበራዊ ልማት ላይ በመሳተፍም የህዝብ ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ አጋር አካላቱ እገዛ እያደረጉ መሆኑንም ጠቁመዋል። የዚሁ ማሳያ የሆነው አልማኮን በአዲስ ብራንድ መምጣቱ የተሰጠውን ተልእኮ በብቃት በመፈጸም የክልሉን እድገት ለማፋጠንና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የበኩሉን ድርሻ ይብልጥ እንዲያጠናክር ያደርገዋል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም በክልል የሚገኙ የልማት ድርጅቶች በክልሉ እድገት ውስጥ ያላቸውን አበርክቶ እንዲያጠናክሩም ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን ነው የገለጹት። የአማራ ልማት ማህበር /አልማ/ ዋና ስራ አስፈጻሚና የአልማኮን ዳይሬክተሮች ቦርድ ሰብሳቢ አቶ መላኩ ፈንታ በበኩላቸው ፤ ማህበሩ ሀብት የሚያመነጩ ተቋማትን በማቋቋም ከእርዳታ ጠባቂነት ለመውጣት እየሰራ ይገኛል። አልማኮን የተሰኝው ተቋምም በኮንስትራክሽን፣ በሪል እስቴት ልማትና በግንባታ ግብዓት አቅርቦት ላይ እየሰራ እንደሚገኝም ነው ያመለከቱት። ኩባንያው በአዲስ ብራንድ መምጣቱም በኮንስታራክሽንና በኢንዱስትሪው ዘርፍ ተወዳዳሪ ምርቶችን ይዞ ወደ ገበያ በመግባት የክልሉን እድገት ለፋጠን የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት እንደሚያስችለው አስረድተዋል። የአልማኮን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሰጥቷል ደሳለኝ እንደገለጹት፤ ኩባንያው በ2005 ጀምሮ በኮንስትራክሽን ዘርፉ በመሰማራት ለክልሉ እድገትና ለህዝቡ ተጠቃሚነት የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ኩባንያው አዲስ ብራንድ ይዞ መምጣቱም በአምስት ዓመት ስትራቴጅክ እቅዱ መሰረት አዲስ አደረጃጀትና አሰራር በመፍጠር የገበያ አድማሱን ለማስፋት እንደሚያስችለው አስገንዝበዋል። በመደረኩ ላይም በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአማራ ክልል የገጠር ዘርፍ አስተባባሪ ድረሥ ሳህሉ(ዶ/ር)ን ጨምሮ ሌሎች የክልሉ የቢሮ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።    
የመምህራንን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት የክልሉ መንግስት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ ያደርጋል
May 2, 2026 254
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 24/2018(ኢዜአ)፦ የመምህራንን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት የክልሉ መንግስት ቀጣይነት ያለው ድጋፍ እንደሚያደርግ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለፁ፡፡ ‎አቶ ደስታ ሌዳሞ የክልሉ መምህራን ማህበር ለሚያስገነባቸው የመምህራን ሆስፒታል እና ሁለገብ ሕንጻዎች ግንባታ ሥራ የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል፡፡   ርዕሰ መስተዳድሩ በዚህ ወቅት እንዳሉት መምህራን በክልሉ ሁለንተናዊ ዕድገት ላይ ያላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑንና በተለይ ከማህበሩ ጋር በመቀራረብ የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የትምህርት ሥብራትን ለመጠገንና የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ እየተደረገ ባለው ጥረት ተጨባጭ ለውጥ እየታየ መምጣቱንም ተናግረዋል፡፡ የክልሉ መንግስት ለግንባታ ሥራው ማስጀመሪያ የሚሆን 50 ሚሊየን ብር ድጋፍ ማድረጉንና ሕንፃው ተጠናቆ ለአገልግሎት እስኪበቃ የክልሉ መንግስት ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡   የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንት ዮሐንስ በንቲ (ዶ/ር) በበኩላቸው መምህራን በትውልድ ግንባታ ውስጥ ተሳትፏቸው ከፍተኛ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ የመምህራን ኢኮኖሚያዊ አቅም እንዲሻሻል፣ ምቹ የሥራ አካባቢ እንዲኖራቸውና ጤናቸው በአግባቡ ተጠብቆ በበለጠ ትጋት እንዲሰሩ ለማስቻል ማህበሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ ፕሮጀክት ቀርጾ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   የሲዳማ ክልል መምህራን ማህበር ፕሬዚዳንት ኢያሱ ፍቅሬ የክልሉ መምህራን ጠንካራ የትምህርት ሥርዓትን ለመገንባትና የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ከመንግስት ጋር በቅንጅት እየሰሩ ይገኛሉ ብለዋል። ማህበሩ ከ46 ሺህ በላይ አባላትን በሥሩ መያዙን ጠቁመው የመምህራን መታከሚያ ሆስፒታልና ሁለገብ ሕንጻዎቹ የረጅም ጊዜ ጥያቄ ሆነው መቆየታቸውን አስታውሰዋል፡፡ በክልሉ በየደረጃው በመንግስት እየተደረገላቸው ላለው ያልተቋረጠ ድጋፍ አመስግነው የማህበሩ አባላት ትውልድ የመቅረጽ ሀላፊነታቸውን በበለጠ ተናሳሽነትና ትጋት አጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። ለመምህራን ሆስፒታል የሚገነባው ሕንጻ ባለ 6 ወለል መሆኑን ገልጸው፣ ሁለገብ ሕንጻው ባለ 12 ፎቅ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሕንጻዎቹ በ1ሺህ 200 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ እንደሚያርፉ ገልጸው ለግንባታቸውም በአጠቃላይ ከ900 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ እንደሚጠይቁ ገልጸዋል።
አርሶ አደሮች ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በወቅቱ መቅረቡ ለግብርና ሥራቸው ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን ተናገሩ
May 2, 2026 85
ወልቂጤ፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- ለበልግ ወቅት አዝመራ የአፈር ማዳበሪያ እና ምርጥ ዘር በወቅቱ ማግኘታቸው ለግብርና ሥራቸው ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን ኢዜአ ያነጋገራቸው የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ።   የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር ወቅቱን ጠብቆ መቅረቡ ለግብርና ልማት ሥራቸው መሳካት ከፍተኛ ዐቅም መፍጠሩን የአበሽጌ ወረዳ አርሶ አደር ሰብስቤ ወልደሃዋርያት ተናግረዋል። ከአራት ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ማግኘታቸውን ገልጸው፤ እስካሁንም ሦስት ሄክታር መሬታቸውን በበቆሎ እና በማሽላ ምርጥ ዘር መሸፈናቸውን አስረድተዋል።   አርሶ አደር ፍቃደ ተበቃም የቀረበላቸውን የአፈር ማዳበሪያ ተጠቅመው ማሳቸውን በበቆሎ ዘር እንደሸፈኑ ገልጸዋል።   በዞኑ ከ82 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበልግ አዝመራ በዘር ለመሸፈን ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አበራ ወንድሙ ናቸው። በበልግ እርሻ በቆሎ፣ ማሽላ፣ ድንችና ሌሎች ሰብሎች እንደሚለሙ ጠቅሰው፤ እስካሁን 34 ሺህ ሄክታር ማሳ በድንች ዘር መሸፈኑን አረጋግጠዋል። በ46 ሺህ ሄክታር ላይ በቆሎ እንደሚለማ ጠቁመው፤ በግንባር ቀደም አርሶ አደሮችም በሄክታር ከ121 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ግብ ተጥሏል ብለዋል። የበልግ አዝመራ ልማቱን ለማሳካት 8 ሺህ 200 ኩንታል የበቆሎ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ ቀመቅረቡን ጠቁመዋል። ከሰው ሠራሽ ማዳበሪያ በተጨማሪ የተፈጥሮ ማዳበሪያ (ኮምፖስት) ተዘጋጅቶ ለግብርና ሥራው ጥቅም ላይ እየዋለ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
መንግሥት ሀገራዊ ብልፅግናን የሚያፋጥኑ መዋቅራዊ ለውጦችን በስኬት እያከናወነ ይገኛል -የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
May 2, 2026 83
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 24/2018 (ኢዜአ)፦ መንግሥት ዘላቂ አጀንዳዎች ላይ በማተኮር ሀገራዊ ብልፅግናን የሚያፋጥኑ መዋቅራዊ ለውጦችን በስኬት እያከናወነ እንደሚገኝ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ገለጸ። አገልግሎቱ ባወጣው መግለጫ፤ መንግሥት የ'ዲጂታል ኢትዮጵያ'ን መነሻ ያደረገውና ግልጽነትን ያሰፈነው ዘመናዊ የመንግሥት አገልግሎት ሥርዓት በተግባር ፍሬ እያፈራ ያለ ታላቅ ሀገራዊ ሽግግር ነው ብሏል። በተለይም የቴሌኮም ዘርፍ ሊበራላይዜሽን ርምጃዎች የውድድር መንፈስን በመፍጠር የኢንተርኔትና የዲጂታል ትስስር ተደራሽነትን በከፍተኛ ፍጥነት ማሳደግ መቻሉን አመልክቷል። ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ፍትህን ለማስፈን ወሳኝ የሆነው የ"ፋይዳ" ብሔራዊ የዲጂታል መታወቂያ ሥርዓትም በተሳካ ሁኔታ በመተግበር ላይ ይገኛልም ነው ያለው። ይህ ሥርዓት በአጭር ጊዜ ውስጥ በሚሊየን የሚቆጠሩ ዜጎችን ተጠቃሚ በማድረግ የፋይናንስ አካታችነትን ከማረጋገጡም በላይ የመንግሥትን ሀብት ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ለማከፋፈል እና ድጋፍ ለሚሹ የሕብረተሰብ ክፍሎች በቀጥታ እንዲደርስ በማድረግ ረገድ የላቀ አስተዋፅዖ የሚያበረክት ዳግማዊ ሕዳሴያችን ነው ሲልም አብራርቷል። የዜጎችን እንግልት ለማስቀረት እና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን የመንግሥት አገልግሎቶችን ወደ ዲጂታል አማራጭ የማሸጋገሩ ጥረት ሌላው ተጨባጭ ስኬት የተመዘገበበት መስክ ነው ያለው መግለጫው፤ የተለያዩ የሚኒስቴሮች የፌዴራል ተቋማት አገልግሎቶቻቸውን በኤሌክትሮኒክስ መንገዶች መስጠት በመጀመራቸው የቢሮክራሲ ውጣ ውረዶች በከፍተኛ ደረጃ እንዲቀንሱ ተደርጓል ብሏል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ የመንግሥት ክፍያዎችን በዲጂታል የክፍያ ሥርዓቶች እንዲፈጸሙ መደረጉ የምዝበራና የሙስና ቀዳዳዎችን በመዝጋት፣ የመንግሥትን ገቢ በከፍተኛ መጠን ለማሳደግ እና ሀብትን ለልማት ስራዎች ለማዋል አስቻይ ዐውድ መፍጠር አስችሏል። ለዚህ የዲጂታል ሽግግር የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ዋነኛ ምሰሶ ሲሆን፤ ዘርፉ በተለይም ለወጣቱ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ አስረድቷል። በቴክኖሎጂ ፈጠራ ላይ ለተሰማሩ ወጣቶች (ስታርትአፖች) ምቹ ምህዳር ከመፍጠር አኳያ የሕግ ማዕቀፎች መሻሻላቸው እና የፋይናንስ አቅርቦት አማራጮች መስፋፋታቸው ኢትዮጵያ በቀጣይ ዓመታት የአፍሪካ የቴክኖሎጂ ማዕከል እንድትሆን ጠንካራ መሰረት ጥሏልም ነው ያለው አገልግሎቱ በመግለጫው። መንግሥት ለዘርፉ የሰጠው ልዩ ትኩረት ዓለም አቀፍ የቴክኖሎጂ ኩባንያዎችን ትኩረት ስቦ ቀጥተኛ የውጭ ኢንቨስትመንትን በመሳብ ረገድ አበረታች ውጤቶች እያስመዘገበ መቀጠሉንም አመልክቷል።
ኢንተርፕራይዞቹ በሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው
May 2, 2026 142
ሆሳዕና፤ ሚያዝያ 24/2018 (ኢዜአ)፡- በመንግሥት የተደረገላቸው ድጋፍ ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር እንዳስቻላቸው በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተለያየ የሥራ መስክ የተደራጁ ኢንተርፕራይዞች ገለፁ፡፡   በጉራጌ ዞን አረቅጥ ከተማ የወሄነት ዳቦ ማምረቻና መሸጫ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ወጣት መሰረት ወልዴ እንዳለችው፤ ኢንተርፕራይዛቸው ከአባላቱ አልፎ ለሌሎች ወጣቶች የሥራ ዕድል መፍጠር ችሏል። ከሦስት ዓመት በፊት በመንግሥት በተመቻቸላችው የ50 ሺህ ብር ብድር የማምረቻና የመሸጫ ሼድን ጨምሮ በተሰጣቸው የሥልጠና ድጋፍ ወደ ሥራ መግባታቸውን አውስታለች። ማኅበሩ አሁን ላይ የአባላቱን ተጠቃሚነት ከማሳደግ አልፎ፤ ለ 25 ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን እና ከ11 ሚሊየን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገቡን ለኢዜአ አረጋግጣለች።   በቡታጅራ ከተማ የሚገኘው የአድማሱ ቶርኖ ሥራዎች አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ሥራ አስኪያጅ ወጣት ዳዊት አድማሱ፤ ኢንተርፕራይዙ የአርሶ አደሩን ምርት አሰባሰብ ሂደት የሚያዘምኑ ማሽኖችን መሥራቱን ገልጿል። ምርቱን ለገበያ በማቅረብ ከመጠቀማቸው አልፎ፤ ለ13 ወጣቶችም የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ተናግሯል። ኢንተርፕራይዙ በ300 ሺህ ብር ሠራ መጀመሩን አውስቶ፤ አሁን ላይ ካፒታሉ 5 ሚሊየን ብር ደርሷል ብሏል።   የውኃ መሳቢያ ፓምፕ እና ሌሎች የፈጠራ ሥራዎችን ለገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን የገለጸው ደግሞ በሆሳዕና ከተማ የሚገኘው የአሚቼ ብረታ ብረትና እንጨት ሥራዎች ቴክኖሎጂ ሽግግር አነስተኛ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ተካልኝ ዓለሙ ነው። በተሰማሩበት ዘርፍ ተጠቃሚነታቸው እያደገ ከመምጣቱ በተጨማሪ በቴክኖሎጂ ሽግግር ረገድ ሌሎች ወጣቶችን እያሰለጠኑ መሆኑንም አስታውቋል። በክልሉ የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሙስጠፋ ኢሳ እንዳሉት፤ በአነስተኛ እና በመካከለኛ ደረጃ ለሚገኙ 3 ሺህ 620 አምራች ኢንተርፕራይዞች ድጋፍና ክትትል እየተደረገ ነው። ኢንተርፕራይዞቹ ዘላቂና አስተማማኝ የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ ለሀገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት የሚያበረክቱት አስተዋጽዖ ከፍተኛ መሆኑንም አመላክተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም