ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በክልሉ ጥራትና ደህንነቱ የተረጋገጠ ከ169 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር እየተሰራጨ ነው 
Apr 29, 2026 86
ባህርዳር ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ለ2018/19 የምርት ዘመን ጥራትና ደህንነቱ የተረጋገጠ ከ169 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑን የክልሉ የግብርና ጥራትና ደህንነት ባለስልጣን አስታወቀ። ‎የባለስልጣኑ ምክትል ኃላፊ አቶ ዘላለም ልየው ለኢዜአ እንደገለፁት፤ጥራትና ደህንነቱ በላብራቶሪ የተረጋገጠ ዘር ለአርሶ አደሩ ተደራሽ በማድረግ የክልሉን ምርታማነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው።   በዚህም ለ2018/2019 የምርት ዘመን ጥቅም ላይ የሚውል ከ169 ሺህ ኩንታል በላይ የበቆሎ፣ ስንዴ፣ ማሽላ፣ ጤፍና ሌሎች የሰብል ዘር ጥራትና ደህንነት በላብራቶሪ በማረጋገጥ እየተሰራጨ መሆኑን ገልጸዋል። የዘር ጥራትና ቁጥጥር ስራው የተካሄደው በአማራ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝ፣ በግብርና ስራዎች ኮርፖሬሽን፣ በዩኒየኖችና በግል ዘር አብዢዎች የቀረበውን መሆኑን ጠቅሰዋል።   የዘር ጥራትና ደህንነቱ በላብራቶሪ ተፈትሾና ተረጋግጦ በህብረት ስራ ማህበራትና በዘር አብዢዎች አማካኝነት ለአርሶ አደሩ የሚሰራጨው ምርጥ ዘርም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ጠቀሜታው የጎላ ነው ብለዋል። አርሶ አደሩም ጥራትና ደህንነቱ የተረጋገጠ ዘር ገዝቶ በመጠቀም ምርታማነቱን በማሳደግ የምግብ ሉዓላዊነቱን ለማረጋገጥ እንዲሰራ መክረዋል።   ‎የክልሉ ግብርና ቢሮ የዘር ብዜት ባለሙያ አቶ ጥላዬ ሞገሴ እንዳሉት ከባለስልጣኑ ጋር በመተባበር ለአርሶ አደሩ የሚቀርበውን ዘር ጥራት በማረጋገጥ ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት እየተሰራ ነው። በዚህም አርሶ አደሩ በህገወጥ መንገድ ዘርን ገዝቶ እንዳይጠቀም ተከታታይ ትምህርት በባለሙያዎች እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ በዘንድሮው የመኸር አዝመራ ከ5 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች በዘር እንደሚሸፈን ከክልሉ ግብርና ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በዞኑ ቋሚ ፍራፍሬን በኩታ ገጠም በማልማት አርሶ አደሩን በዘላቂነት ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው
Apr 29, 2026 150
ደሴ ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ወሎ ዞን በኩታገጠም ቋሚ ፍራፍሬን በማልማት የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በዞኑ እስከ ሐምሌ 30/2018 የሚዘልቅ 900 ሄክታር መሬት በኩታ ገጠም እርሻ ፍራፍሬን ለማልማት የሚያስችል የችግኝ ተከላ ዘመቻ ተጀምሯል። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አህመድ ጋሎ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ዞኑ የፍራፍሬ ችግኝ ተከላውን የሚያካሔደው ተስማሚ ስነ-ምህዳርና የአየር ንብረት ባላቸው አምስት ወረዳዎች ነው። በዚህ የዘመቻ ስራ አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ሙዝ፣ ብርቱካንና ሌሎች ቋሚ የፍራፍሬ ችግኞችን የመትከል ስራ እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል።   የችግኝ ተከላው በተሁለደሬ፣ በአምባሰል፣ በቃሉ፣ በወረባቦና በአርጎባ ብሔረሰብ ወረዳዎች እየተከናወነ ነው። ይህም በዘልማድና በተበታተነ አግባብ የሚካሔዱ የፍራፍሬ ልማት ስራዎችን በማስቀረት የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በአጭር ጊዜ ምርት የሚሰጥ፣ በሽታን የሚከላከልና ምርታማ የፍራፍሬ ችግኝ ለአርሶ አደሩ እየቀረበለት እንደሚገኝም ነው የገለጹት። በተለይ በሎጎ ሀይቅ ሪዞርት ዙሪያ የለማው የፍራፍሬ ልማት ውጤታማ በመሆኑ በአርሶ አደሩ ዘንድ ከፍተኛ መነሳሳትን መፍጠሩን ነው የገለጹት።   በተሁለደሬ ወረዳ የ012 ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሰይድ ፈንታ እንዳሉት ፣ በሎጎ ሀይቅ ሪዞርት ዙሪያ የለማው የፍራፍሬ ተክል በአጭር ጊዜ ምርት ሲሰጥ መመልከቴ መነሳሳትን ፈጥሮብኛል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም በግማሽ ሄክታር ማሳቸው ላይ ከ100 በላይ የተሻሻሉ የሙዝ ችግኞትን መትከላቸውን ገልጸዋል።   የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መሀመድ አደም በበኩላቸው፣ በተፈጠረላቸው ግንዛቤ መሰረትም ቋሚ የሆኑ ፍራፍሬዎችን እያለሙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በጫት ተሸፍኖ የነበረውን ሩብ ሄክታር መሬታቸውን በመመንጠርም ፓፓያና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞችን እየተከሉ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ሉባባ ሰይድ ናቸው።   በደቡብ ወሎ ዞን በመጪው ክረምት በ3 ሺህ 700 ሄክታር መሬት ላይ የፍራፍሬ ችግኝ ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ከዞኑ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
የመስሪያ ቦታና የመሰረተ ልማት አቅርቦት መኖሩ በተሰማራንበት ዘርፍ ውጤታማ አድርጎናል- አምራች ኢንዱስትሪዎች
Apr 29, 2026 166
ሀዋሳ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦መንግስት ባደረገላቸው የመስሪያ ቦታና የተሳለጠ የመሰረተ ልማት አቅርቦት በተሰማሩበት መስክ ውጤታማ መሆናቸውን አምራች ኢንዱስትሪዎች ገለጹ፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ350 ሚሊዮን ዶላር በላይ ተኪና የወጪ ምርት በክልሉ በሚገኙ አምራች ኢንዱስትሪዎች በኩል መመረቱን የክልሉ ኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ገልጿል፡፡ የአምራች ኢንዱስትሪዎቹ የስራ ኃላፊዎች ለኢዜአ እንደገለፁት፤ መንግስት የመስሪያ ቦታና የተሳለጠ የመሰረተ ልማት አቅርቦት እንዲኖር ማድረጉ በተሰማሩበት ዘርፍ ውጤታማ እንዲሆኑ እያደረገ ነው። በሀዋሳ ከተማ በፎምና በቴራዞ ምርት የተሰማሩት አምራች ኢንዱስትሪ ስራ አስኪያጆች አቶ ዘሪሁን ሀይለማሪያም እና አቶ አዲስ አበበ፤ መንግስት የመስሪያ ቦታ፣የኃይልና ሌሎች አቅርቦቶች በማመቻቸቱ በአጭር ጊዜ ውጤታማ እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡ በአንድ ላይ 230 ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል እንደፈጠሩ የሚገልጹት አምራች ኢንዱስትሪዎቹ ከውጭ የሚገባውን ምርት በመተካት ረገድ ውጤታማ ስራ እየሰሩ መሆኑን አመልክተዋል። የኩል ፕላስቲክ ሪሳይክሊንግ ኢንተርፕራይዝ ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ ሰላማዊት ቶማስ በበኩላቸው፤ መንግስት እያደረገ ያለው ድጋፍ ተኪ ምርት በማምረት ስኬታማ እንዲሆኑ ማድረጉን አስረድተዋል፡፡ በአምራች ኢንዱስትሪዎቹ የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ዜጎች መካከል ወጣት ሰለሞን ጋሻው በተፈጠረለት የስራ ዕድል ቤተሰቡን እያስተዳደረ እንደሚገኝ ነው የገለጸው። ባገኘው የስራ ዕድልም ከሚያገኘው ገቢ በተጨማሪ የዕውቀት ሽግግር ዕድል ማግኘቱንም ተናግሯል። የሲዳማ ክልል የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አሻግሬ ጀንበሬ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤በክልሉ በወጪና ተኪ ምርቶች ላይ የተሰማሩ አምራች ኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅምን ለማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎች በተቀናጀ መንገድ እየተከናወኑ ነው፡፡ በተለይም የኤሌክትሪክ ኃይል፣ ጥሬ ዕቃ፣ የተማረ የሰው ኃይልና ሌሎች አቅርቦቶችን በማመቻቸትና በምርታማነት ሂደት የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለቅሞ ለመፍታት የተወሰዱ እርምጃዎች ውጤት ማምጣታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም በክልሉ የኢንዱስትሪዎች የማምረት አቅም ከ65 በመቶ በላይ ዕድገት ማሳየቱን ጠቁመው ባለፉት ዘጠኝ ወራት ወደ ውጭ ከተላኩ ምርቶች ከ120 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ተገኝቷል ነው ያሉት። በዚህም ከ230 ሚሊዮን ዶላር በላይ የሚያወጣ ምርት መተካት መቻሉን ተናግረዋል፡፡
መንግሥት የዜጎችን የኑሮ ጫና ለመቀነስ በርካታ ቢሊዮን ብሮችን በመመደብ እና አመራጮችን ሁሉ አሟጦ በመጠቀም የነዳጅ አቅርቦትን አስቀጥሏል
Apr 29, 2026 260
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መንግሥት የዜጎችን የኑሮ ጫና ለመቀነስ በርካታ ቢሊዮን ብሮችን በመመደብ እና አማራጮችን ሁሉ አሟጦ በመጠቀም የነዳጅ አቅርቦትን ማስቀጠሉን የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ። መንግሥት በመሠረታዊ ፍላጎቶቿ በራሷ የምታሟላ ሉዓላዊ ሀገር ለመፍጠር ፖሊሲ ቀርጾ እየሠራ ይገኛል። በተለይም ከነዳጅ ጥገኝነት ለመላቀቅ ቀድሞ ወደ ሥራ መግባቱ፣ በሀገር ላይ ይደርስ የነበረን የከፋ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ከሌሎች ሀገራት አንጻር በከፍተኛ ደረጃ ማስቀረት እንደቻለ ገልጿል። ምንም እንኳ ሙሉ ለሙሉ ከነዳጅ ጥገኝነት ለመላቀቅ ገና ሰፊ የመንግሥት እና የግሉ ዘርፍ ጥረት ቢጠይቅም፣ ባለፉት ስምንት ዓመታት በታዳሽ የኃይል ዘርፍ አቅርቦት ላይ የተሠራው ሥራ አሁን ያለውን ቀውስ ለመቋቋም በእጅጉ ማገዙን አመልክቷል። የኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ሙሉ በሙሉ ከታዳሽ የኃይል ምንጮች ማለትም ከውኃ፣ ከነፋስ እና ከፀሐይ የሚገኝ ሲሆን፤ በቀጣይም ከጂኦተርማል እና ከኑክሊየር ኃይል በማመንጨት የሀገሪቱን ፍላጎት በአስተማማኝ ደረጃ ለማሟላት እየተሠራ ይገኛልም ነው ያለው አገልግሎቱ። የኃይል ምንጮችን ታዳሽ ማድረግ መቻሉ፣ አሁን ካጋጠመው ዓለም አቀፍ የነዳጅ እጥረትና የዋጋ መናር ጋር ተያይዞ በሀገሪቱ አምራች ኢንዱስትሪዎች ላይ ሊከሰት ይችል የነበረን ጫና ማስቀረት ማስቻሉን ገልጿል። መንግሥት ላለፉት ዓመታት ዜጎች የታዳሽ ኃይል አማራጮችን እንዲጠቀሙ የተለያዩ የማበረታቻ ሥርዓቶችን ተግባራዊ አድርጓል። በዚህም የመንግሥትን አቅጣጫ በመቀበል የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን መጠቀም የጀመሩ ዜጎች አሁን ላይ የችግሩ ሰለባ አለመሆናቸውን መረጃው አመላክቷል። ይህም ለዘገዩት ትምህርት የሚሰጥ ሲሆን፣ ለመንግሥት ደግሞ ለሚከተለው የፖሊሲ አቅጣጫ ትክክለኛነት በራስ መተማመን የሚፈጥር እንደሆነም ተነስቷል። በአሁኑ ወቅት ከ140 ሺህ ያላነሱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚገኙ ሲሆን፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ይህንን መጠን በብዙ እጥፍ ለማሳደግ ታቅዶ እየተሠራ መሆኑን አገልግሎቱ ጠቁሟል። መንግሥት የኃይል ሉዓላዊነትን በታዳሽ የኃይል ምንጮች ላይ ተመሥርቶ ለማረጋገጥ ጥረት እያደረገ ነው። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ የኢትዮጵያን የኃይል አቅርቦት በከፍተኛ ደረጃ ሲያሳድገው፣ የነፋስ ኃይል ማመንጫዎችም በየጊዜው እየተመረቁ ወደ ሥራ እየገቡ ይገኛሉ። በአፍሪካ ግዙፍ የፀሐይ ኃይል ማመንጫ ሶላር ፓኔሎችን የማምረት አቅም የተፈጠረ ሲሆን፣ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎም እየተበረታታ እንደሚገኝም ተነስቷል። በተጨማሪም የነዳጅ ማጣሪያ እና የተፈጥሮ ጋዝ ማምረቻ ፋብሪካዎች ግንባታ እየተፋጠነ መሆኑ ተጠቁሟል። በእነዚህ ሁሉ ጥረቶች መካከል አሁን ያጋጠመው ዓለም አቀፍ ቀውስ በዜጎች ላይ የከፋ ጉዳት እንዳያደርስ ለመከላከል፣ መንግሥት ቀደም ሲል ሲደጉም ከነበረው በተጨማሪ በየወሩ 20 ቢሊዮን ብር በመደጎም እና የተለያዩ አማራጮችን በመጠቀም የነዳጅ አቅርቦትን እያስቀጠለ እንደሚገኝ አገልግሎቱ አስታውቋል። መንግሥት በአረንጓዴ የኢኮኖሚ ፖሊሲ አቅጣጫ አማካኝነት ችግሩን በዘላቂነት ከሕዝቡ ጋር እንደሚሻገረው እና የመውጫ በሩም ከቅርብ ርቀት ይታያል ሲል አገልግሎቱ በመረጃው አመላክቷል።
በጅማ ዞን የመኸር ወቅት እርሻ ስራ ተጀምሯል
Apr 29, 2026 105
ጅማ ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በጅማ ዞን በመኸር ወቅት 883 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ታቅዶ የእርሻ ስራ መጀመሩን የዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት አስታወቀ። የፅህፈት ቤቱ ሀላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም ለኢዜአ እንደገለጹት በዞኑ ግብርናውን በማስፋትና በማዘመን ምርትና ማርታማነትን ለማሳደግ በተሰጠ ትኩረት አበረታች ውጤት እየተገኘ ነው።   በተያዘው 2018/19 ምርት ዘመን በመኽር ወቅት 883 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተለያዩ ሰብሎች በማልማት 36 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ተናግረዋል። እስካሁንም በምርት ወቅቱ ከሚለማው አጠቃላይ መሬት ውስጥ 13 በመቶ የሚሆነው ታርሶ ቀድመው በሚዘሩ በቆሎና ማሽላ ሰብሎች ዘር መሸፈኑን ጠቅሰዋል። ለምርት ወቅቱ ለምርት ማሳደጊያ የሚያስፈልገው ግብአት በወቅቱ ለአርሶ አደሩ እየቀረበ መሆኑን ጠቁመው እስካሁንም ከ780 ሺህ ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ገብቶ ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑን አመልክተዋል ። በተጨማሪም 21 ሺህ ኩንታል ምርጥ ዘር እየቀረበ መሆኑን ጠቁመው ግብአቱ ከወዲሁ መቅረቡ ወቅቱን የጠበቀ የዘር ስራ ለማካሄድ ማገዙን ተናግረዋል። በቀጣይም የክረምቱን ዝናብ በመጠቀም ጤፍ እና ሩዝን ጨምሮ ሌሎችም የሰብል አይነቶች እንደሚዘሩ አመላክተዋል።   መንግስት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየተገበራቸው ያለው የተለያዩ የግብርና ኢኒቬቲቮች ውጤት እያመጡ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዞኑ ከለውጡ በኋላ ግብርናውን ለማዘመን በ20 ወረዳዎች 1ሺህ 426 ትራክተሮች ለአርሶ አደሩ ቀርበው እየተሰራባቸው መሆኑንም አስታውቀዋል ። በዞኑ ቀርሳ ወረዳ ነዋሪዎች አርሶ አደር ሙሀመድ አባቦር እና መሀመድ ኑር አባተማም በሰጡት አስተያየት አስፈላጊ የግብርና ግብቶችን ቀድመው በመውሰዳቸው መሬታቸውን በዘር መሸፈን ጀምረዋል። በግብርና ባለሙያዎች ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑን ጠቁመው ከአምናው የተሻለ ምርት ለማግኘት አቅደው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል ። በዞኑ በመኽር ወቅት እርሻው ከ420 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች እንደሚሳተፉ ታውቋል።
መንግስት የናፍጣ የአቅርቦት መጠን ከዛሬ ጀምሮ ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት ወደነበረበት እንዲመለስ ወሰነ
Apr 29, 2026 381
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ መንግስት የናፍጣ ነዳጅ የአቅርቦት መጠን ከዛሬ ጀምሮ ከመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በፊት ወደነበረበት እንዲመለስ መወሰኑን የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ገለጹ፡፡ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ወቅታዊ የዓለም የነዳጅ ሁኔታን በማስመልከት ለመገናኛ ብዙኅን ማብራሪያ ሰጥተዋል። የገንዘብ ሚኒስትሩ በመግለጫቸው፤ የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በዓለም የነዳጅ አቅርቦትና ዋጋ ላይ ከፍተኛ ጫና መፍጠሩን አብራርተዋል። በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ነዳጅ ሙሉ በሙሉ ከውጭ የሚያስገቡ ሀገራት በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚፈተኑ ገልጸዋል፡፡ መንግሥት የተከሰተው ዓለም አቀፍ የነዳጅ አቅርቦት ችግር በዜጎች ኑሮ ላይ የጎላ ጫና እንዳይፈጥር ተቋማትን በማቀናጀትና የ24 ሰዓት የመከታተያ ክፍል በማቋቋም ክትትል ሲያደርግ መቆየቱን አስታውሰዋል፡፡ በዚህም መንግስት በአጣዳፊ ግዥ የቤንዚንና የአውሮፕላን ነዳጅ በመግዛት ችግሩን መቋቋም የሚያስችል አስተማማኝ ሥራ መስራቱን ተናግረዋል፡፡ መንግሥት ከጦርነቱ በፊት በቀን 9 ሚሊዮን ሊትር ናፍጣ ያቀርብ እንደነበር አስረድተዋል። ከጦርነቱ በኋላም የነዳጅ ዲፖዎችን ለመሙላትና የኢኮኖሚ ቁጠባን ለማረጋገጥ አቅርቦቱ በቀን ወደ 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሊትር ዝቅ እንዲል ማድረጉን ተናግረዋል። ይሁን እንጂ ወቅቱ የግብርና ግብዓትና ሥራዎችን በከፍተኛ ሁኔታ ማከናወን፣ የውጭ ንግድ ማቀላጠፍ፣ ነዳጅን እንደ ግብዓት የሚጠቀሙ አምራች ዘርፎች እጥረት እንዳይገጥማቸው የተለያዩ ፕሮጀክቶች ጫና እንዳይፈጠርባቸው በማሰብ አቅርቦቱ እንዲሻሻል ተደርጓል ብለዋል። በመሆኑም ከዛሬ ጀምሮ በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የናፍጣ አቅርቦት ከጦርነቱ በፊት ወደ ነበረበት በቀን ዘጠኝ ሚሊዮን ሊትር እንዲመለስ መወሰኑን ገልጸዋል። መንግሥት ጦርነቱን ተከትሎ በወር እስከ 20 ቢሊዮን ብር ተጨማሪ ድጎማ እያደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ አጠቃላይ የድጎማ ክምችቱ 300 ቢሊዮን ብር መድረሱን አስታውቀዋል። የመሰረታዊ የሸቀጥ አቅርቦትን አስተማማኝ ለማድረግም ከፍተኛ ሥራ በመስራት የዜጎችን የኑሮ ጫና እየፈታ ቀጣይነት ያለው ፈጣን ዕድገት ማስመዝገብ እየተቻለ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የዓለም የነዳጅ አቅርቦት ሰንሰለት በከፍተኛ ሁኔታ በተጎዳበት ወቅትም በልዩ ግዥ፣ በከፍተኛ ድጎማና በከፍተኛ ዋጋ እየቀረበ መሆኑን ተናግረዋል። መንግሥት ነዳጅ በልዩ ግዥና በከፍተኛ ወጭ እያቀረበ ባለበት ወቅት አሻጥር በመፍጠር በሕገ-ወጥ ሥራ ላይ የሚሰማሩ አካላትን መቆጣጠር እንደሚገባም አሳስበዋል። በመሆኑም ህብረተሰቡ ከጸጥታና ሌሎች የመንግስት ተቋማት ጋር በመተባበር በሕገ-ወጥ ድርጊት ላይ የሚሳተፉ አካላትን በመቆጣጠር ትብብር እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።
መንግስት ለማዕድን ዘርፍ የሰጠው ትኩረት ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጣ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ 
Apr 28, 2026 409
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፦ መንግስት ለማዕድን ዘርፍ የሰጠው ትኩረት ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጣ እንደሚገኝ ምክትል ጠቅላይ ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የማዕድን ሀብት በማልማትና ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት በማዋል ረገድ ወደ ተጨባጭ ተግባር መሸጋገሯን አመልክተዋል።   በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግራናይት የሚያመርተውን የኦርላመንት (3ኤም) ማርብልና ቴራዞ ማኑፋክቸሪንግ የሥራ እንቅስቃሴ መመልከታቸውን ጠቁመዋል። ፋብሪካው በክልሉ የሚገኘውን ባለ ብዙ ቀለም የግራናይት ማዕድን በመጠቀም ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ምርት ለገበያ እያቀረበ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ለአካባቢው ማህበረሰብም የሥራ ዕድል ከመፍጠሩ ባሻገር የሀገር ውስጥ ፍላጎትን በመሸፈን የውጭ ምንዛሬን እንደሚያድንም ነው ያብራሩት።   መንግሥት የግሉ ዘርፍ በማዕድን ልማት ላይ በስፋት እንዲሳተፍ የፈጠረው ምቹ ሁኔታ፣ ማበረታቻና ድጋፍ ዛሬ ላይ እንዲህ ያሉ ተጨባጭ ውጤቶችን እያመጣ ነው ብለዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከወርቅ እስከ ግራናይት በተፈጥሮ የታደለ መሆኑን የገለጹት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ይህንን ፀጋ ለሀገር ብልጽግና ለማዋል የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ይበልጥ እንዲጠናከሩ የፌደራል መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረጉን እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
የትራንስፖርት አገልግሎትን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ተግባራዊ የተደረጉ ስልቶች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ ነው 
Apr 28, 2026 111
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦የትራንስፖርት አገልግሎትን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ተግባራዊ የተደረጉ ስልቶች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር አስታወቀ። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ በረኦ ሀሰን፤ የቻይና ኮሙኒኬሽንስ ኮንስትራክሽን ኩባንያ (CCCC) የገዛቸውን 92 ዘመናዊ የኤሌክትሪክ የጭነት ተሽከርካሪዎች በእንዶዴ ባቡር ጣቢያ በመገኘት ሥራ አስጀምረዋል፡፡   እነዚህ ተሽከርካሪዎች ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ በመሆናቸው፣ መንግሥት ከያዘው የአረንጓዴ ትራንስፖርት ስትራቴጂ ጋር የተጣጣሙ መሆናቸው ተገልጿል። ተሽከርካሪዎቹ ለቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ግንባታ አገልግሎት የሚውሉ መሆኑም በዚሁ ወቅት ተጠቁሟል፡፡ ሚኒስትር ዴኤታው በረኦ ሀሰን በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ መንግሥት የትራንስፖርት ዘርፉን ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ውጤታማ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። በተለይም በሀገሪቱ እየተገነቡ ባሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ላይ የሚሰማሩ ተሽከርካሪዎችና መሣሪያዎች ከነዳጅ ጥገኝነት ለማላቀቅ ተግባራዊ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በስፋት ጥቅም ላይ እንዲውሉ በተዘረጋው አሠራር፣ በአሁኑ ወቅት 17 ድርጅቶች በሀገር ውስጥ የመገጣጠም ሥራ መጀመራቸውን አመልክተዋል። እነዚህ ድርጅቶች ከሁለት እግር ተሽከርካሪዎች ጀምሮ እስከ 400 ኩንታል የመሸከም አቅም ያላቸውን የጭነት ተሽከርካሪዎች እየገጣጠሙ እንደሚገኙም አብራርተዋል። በተጨማሪም የመንግሥት ተቋማትና ዩኒቨርሲቲዎች የሚገዟቸው ተሽከርካሪዎች እንዲሁም የከተማ የሕዝብ ትራንስፖርት ባሶች ሙሉ በሙሉ የኤሌክትሪክ እንዲሆኑ መወሰኑን ጠቅሰዋል። ዘርፉን ይበልጥ ለማበረታታትም ነዳጅ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን ወደ ኤሌክትሪክ ለመቀየር የሚያስፈልጉ የቴክኖሎጂ ግብዓቶች ከቀረጥ ነፃ እንዲገቡ መደረጉን አስታውሰዋል። በዘርፉ የግሉን ተሳትፎ ይበልጥ ማሳደግ የሚያስችሉና የሚያበረታቱ አሰራሮች እየተዘረጉ መሆኑን ገልጸው፤ በዚህም ተጨባጭ ውጤቶች እየመጡ መሆኑን ተናግረዋል። አሁን በቻይናው ተቋራጭ ተገዝተው የገቡት የሲኖ ብራንድ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ከፍተኛ ጥራት ያላቸውና ለሀገሪቱ የአረንጓዴ ልማት ጉዞ ትልቅ አስተዋጽኦ የሚኖራቸው መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡
ከስልጠናው ያገኘነው እውቀት ወቅቱ የሚጠይቀውን ብቁ ማህበራትን ለመፍጠር ያግዘናል-ሰልጣኞች
Apr 28, 2026 147
አሶሳ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ ከስልጠናው ያገኘነው እውቀት ወቅቱ የሚጠይቀውን ብቁ የህብረት ስራ ማህበራትን ለመፍጠር ያግዘናል ሲሉ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የህብረት ስራ ማህበራት አመቻች ባለሙያዎች ተናገሩ። በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ "ወደ ቀበሌ መድረስ " በሚል መሪ ሃሳብ ለህብረት ስራ ማህበራት አመቻች ባለሙያዎች ላለፉት ስምንት ቀናት ሲሰጥ የነበረው ስልጠና ተጠናቋል። የስልጠናው ተሳታፊዎች በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ስልጠናው ህብረት ስራ ማህበራት ላይ እየተስተዋለ ያለውን የአደረጃጀት ችግር በመቅረፍ በአዲስ መልክ ወደ ስራ እንዲገቡ የሚያደርግ ነው። ከሰልጣኞቱ መካከል አቶ አምሳሉ ቀነኒ፤ ስልጠናውን ከፍተኛ ልምድ ባላቸው የዘርፉ ባለሙያዎች መውሰዳቸው ዘርፉን ለመለወጥ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ነው የገለጹት።   በህብረት ስራ ማህበራት ላይ የሚታዩ የአደረጃጀት እና የፋይናንስ አቅርቦት ችግሮችን በማስተካከል ጠንካራ እና ራሳቸውን የሚያስተዳድሩ ማህበራትን ለመፍጠር እንደሚረዳም እንዲሁ። በተጨማሪም ማሕበራቱን በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ በተሻለ መንገድ በቀጥታ ተሳታፊ ለማድረግም ሰፊ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ነው የተናገሩት። በወሰዱት ስልጠና መሠረትም የህብረት ስራ ማህበራቱ በአዲሱ ሪፎርም መሠረት ወደ ስራ እንዲገቡ ለማድረግና አዳዲስ አሰራሮችን ለመተግበር እንደሚሰሩም ነው ያረጋገጡት።   ስልጠናው መሠረታዊ የህብረት ስራ ማህበራትን አሁናዊ ቁመና ከመዳሰስ ባለፈ ኢኮኖሚውን ከማረጋጋት አንፃር ያለውን ክፍተት አሳይቶናል ያሉት ደግሞ ሰልጣኝ አዚዛ አደም ናቸው። የሂሳብ አያያዝ፣ አደረጃጀት እንዲሁም የድጋፍ እና ክትትል ስራዎችን የበለጠ በማጠናከር የህብረት ስራ ማህበራት ሪፎርሙን እንዲተገብሩ የሚያደርግ በመሆኑም ለስኬታማነቱ እንሰራለን ብለዋል። ስልጠናው የህብረት ስራ ማህበራትን አደረጃጀትን በማዘመን እና ከነበሩበት የቆየ አሰራር በማላቀቅ ወቅቱ የሚጠይቀውን ብቁ ማህበራትን ለመፍጠር ያግዛል ያሉት ደግሞ ማሊክ ዩሱፍ ናቸው።   የህብረት ስራ ማህበራት ለህብረተሰቡ ቅርብ በመሆናቸው መሠረታዊ አገልግሎቶችን ተደራሽ በማድረግ ተልዕኳቸውን እንዲወጡ እንሰራለን ነው ያሉት። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መሬትና ህብረት ስራ ማደራጃ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኑረዲን ሙክታር በበኩላቸው፤ ሪፎርሙ የህብረት ስራ ማህበራት ብቁ የሰው ሀይል በመያዝ የኢኮኖሚ አንቀሳቃሽ እንዲሆኑ የሚያደረግ ነው ብለዋል።   በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ ያለው ይህ የህብረት ስራ ማህበራት ንቅናቄ ውጤታማ እንዲሆን አመቻች ባለሙያዎች ያገኙትን ስልጠና በመተግበር ተጨባጭ ለውጥ ማሳየት እንደሚጠበቅባቸው አሳስበዋል። በስልጠናው ላይ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እና አጎራባች ኦሮሚያ ክልል የተውጣጡ ከ4 መቶ በላይ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
የማህበራቱን አደረጃጀት በማዘመን የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመረው የሪፎርም ስራ ይጠናከራል
Apr 28, 2026 205
ሀዋሳ ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ የህብረት ስራ ማህበራትን አደረጃጀት በማዘመን የአርሶና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመረው የሪፎርም ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ተናገሩ። የኢትዮጵያ ህብረት ሥራ ኮሚሽን “ወደ ቀበሌ መድረስ” በሚል መሪ ሃሳብ በተለያዩ ስድስት ከተሞች ሲያካሂድ የቆየውን 2ኛውን ሀገር አቀፍ የህብረት ሥራ ማህበራት ሪፎርም የንቅናቄ መድረክ ዛሬ አጠናቋል። በሀዋሳ በተካሔደው የማጠናቀቂያ መርሃ ግብር ላይ የግብርና ሚኒስትሩ አዲሱ አረጋ በቪዲዮ ኮንፈረንስ ባስተላለፉት መልዕክት እንዳሉት፤ ባለፉት ስምንት ዓመታት በተለያዩ መስኮች የበለጸገችና ህብረ ብሔራዊት ሀገር ለመፍጠር ዘርፈ ብዙ የሪፎርም ስራዎች ተግባራዊ ተደርገዋል። በተከናወኑ ተግባራትም ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ በርካታ ለውጦች እየተመዘገቡ መሆኑን አክለዋል። የመንግስትን፣ የግሉ ዘርፍንና የዜጎችን የካፒታል አቅምና ዕውቀትን ደምሮ የሚይዙት የህብረት ስራ ማህበራት መሆናቸውን በግብርናና ገጠር ልማት ፖሊሲው በግልጽ መቀመጡን ጠቁመዋል። ማህበራቱ ግብርናውን በማሻገር የአርሶና አርብቶ አደሩን ህይወት መቀየር ረገድ ትልቅ አቅም እንዳላቸው ገልፀው የፋይናንስ አቅርቦት ችግርን በመፍታትና የግብይት ሰንሰለቱን በማሳጠር የሸማቹን ህብረተሰብ ሸክም እንደሚያቀሉም አስረድተዋል። በንቅናቄ መድረኩ የተሳተፉት የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ህብረት ስራ ኤጀንሲ የህብረት ስራ ማህበራት ማደራጃና ማስፋፊያ ዳይሬክተር አቶ ቶንጃ ቶማ በበኩላቸው፤ ማህበራቱ ገበያን በማረጋጋት፣ የአርሶ አደሩን ምርታማነት የሚያሳድጉ ግብዓት በማቅረብና በሌሎች ዘርፎች አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው ብለዋል።   በተለይ ባለፉት የለውጥ ዓመታት የማህበራቱን አቅም ለማሳደግ በተደረገ የሪፎርም ስራ በኢኮኖሚው ውስጥ ያላቸው አበርክቶ እንዲያድግ ማድረጉን ተናግረዋል። የኦሮሚያ ክልል ህብረት ስራ ልማት ኤጀንሲ ተወካይ ወይዘሮ ሹሬ እጅቢቾ፤ በክልሉ የህብረት ስራ ማህበራትን አሰራር፣ አደረጃጀትና አገልግሎት አሰጣጥ ላይ በማተኮር ሪፎርም መሰራቱን ገልጸዋል፡፡   በዚህም ጠንካራ ማህበራት እንዲኖሩ አንድ ላይ የማደራጀት ስራ መሰራቱን ጠቅሰው በንቅናቄ መድረኩ የተገኘውን ልምድና እውቀት ተግባራዊ በማድረግ ለማህበራት ውጤታማነት እንደሚሰሩም ተናግረዋል፡፡ የሲዳማ ክልል ህብረት ስራ ኤጀንሲ የህብረት ስራ ማህበራት ማደራጃና ማስፋፊያ ዳይሬክተር አቶ ደምበሎ ዶንጊሶ በበኩላቸው፤ በሪፎርሙ የማህበራቱን ትርፋማነት፣ የአባላት ተጠቃሚነት ከማጎልበት አንጻር ለውጥ ማምጣት ተችሏል ብለዋል።   ከዚህም ባለፈ በአሰራር ስርዓት በአመራርና በአደረጃጀት የጠነከሩና የፋይናንስ አያያዛቸውን ያዘመኑ ማህበራት መፍጠር እንደተቻለ ገልጸው የተገኘውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል የንቅናቄ መድረኩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ነው የገለጹት። ላለፉት ስምንት ቀናት በሀዋሳ ሲካሄድ በቆየው መድረክ ላይ ከሲዳማ፣ ከደቡብ ኢትዮጵያና ከኦሮሚያ ክልል የተውጣጡ 900 የቀበሌ ህብረት ስራ ማህበራት አደረጃጀት ባለሙያዎች ተሳታፊ ሆነዋል።
የከተማዋ የአካባቢ ልማት ፕላን ቴክኖሎጂንና ፈጠራን በማስፋፋት የነዋሪዎችን ህይወት ለማሻሻል ያግዛል
Apr 28, 2026 130
አዳማ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦የአዳማ ከተማ የአካባቢ ልማት ፕላን ቴክኖሎጂንና ፈጠራን በማስፋፋት የነዋሪዎችን ሕይወት ለማሻሻል ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር የከተማዋ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ ገለፁ። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከኦሮሚያ ከተሞች ፕላን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የአካባቢ ልማት ፕላን ተፈፃሚነት ዙሪያ በየደረጃው ካሉ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ጋር ዛሬ መክሯል። የአካባቢ ልማት ፕላን (Local Development Plan - LDP) በአንድ በተወሰነ የከተማ ክፍል ወይም መንደር ውስጥ የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን፣ የመሬት አጠቃቀም እና የመሰረተ ልማት ዝርጋታን በዝርዝር የሚመራ የከተማ ፕላን አይነት ነው። የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ እንደገለጹት፤ የከተማዋ የአካባቢ ልማት ፕላን ቴክኖሎጂንና ፈጠራን በማስፋፋት የነዋሪዎችን ህይወት ለማሻሻል ትልቅ አቅም የሚፈጥር ነው። ፕላኑ መሬትን በአግባቡ ለማስተዳደርና ለማልማት ካለው ፋይዳ በተጨማሪ ለከተማ ግብርና፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለቴክኖሎጂ ልማትና ስማርት አዳማ ኢንሼቲቭ ለማሳካት ተጨማሪ አቅም መሆኑንም ተናግረዋል። የከተማ ፕላኑ የነዋሪውን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ እንደሚያግዝም ገልጸዋል። እንደ ከንቲባው ገለጻ፣ ፕላኑ ከዚህ በፊት የነበሩ የመልካም አስተዳደር እጦት ቅሬታዎችን፣ የመሬት አጠቃቀም ችግሮችና በመሰረተ ልማት ዝርጋታ ያሉ ማነቆዎችን በአግባቡ የፈተሸ ነው።   የኦሮሚያ ከተሞች ፕላን ኢንስቲትዩት ምክትል ዳይሬክተር አቶ ሸለመ አበበ በበኩላቸው፣ ፕላኑ አዳማ ከተማ ሪጂኦ ከተማ ሆና የተደራጀችበትን ዓላማ የሚያሳካ መሆኑን ተናግረዋል። የከተማዋን መዋቅራዊ ፕላን በማዘጋጀት ለመስተዳድሩ በማስረከብ ወደ ትግበራ እንደተገባ ገልጸው፣ የአካባቢ ልማት ፕላን መዋቅራዊ ፕላኑን ውጤታማ ለማድረግ ፋይዳው የላቀ ነው ብለዋል። የአዳማ ከተማን ዕድገትን ለማሳለጥ የተከናወኑ የኮሪደር ልማትና ሌሎች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሰረተ ልማቶችን መሰረት በማድረግ መዋቅራዊ ፕላኑ መሰራቱንም ምክትል ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል። በክልሉ የአዳማ፣ የቢሾፍቱና የሻሸመኔ ከተሞች በሪጂኦ ማዕቀፍ ውስጥ ሆነው ወደ ልማት ሥራ መግባታቸውን አንስተው የጂማ፣ ማያ፣ ሮቤ እና ነቀምት ከተሞች መዋቅራዊና የአካባቢ ልማት ፕላኖችም እየተዘጋጁ መሆኑን ጠቅሰዋል።
የህብረት ሥራ ማህበራት ንቅናቄ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልጽግና ፋይዳው የጎላ ነው
Apr 28, 2026 103
ጅግጀጋ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የህብረት ስራ ማህበራት ሚና የጎላ መሆኑ ተገለጸ። የኢትዮጵያ ኅብረት ሥራ ማህበራት “ወደ ቀበሌ መድረስ” በሚል መሪ ቃል በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ሲያካሄድ የቆየው ሁለተኛው ሀገር አቀፍ የኅብረት ሥራ ሪፎርም ንቅናቄ ዛሬ ተጠናቀቀ።   በማጠቃለያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት በኢትዮጵያ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን የህብረት ሥራ ቴክኖሎጂ ልማትና ማስፋፊያ መሪ ሥራ አስፈፃሚ እና የጅግጅጋ ማዕከል ንቅናቄ አስተባባሪ አንዱአለም አፈወርቅ እንደገለጹት፣ የኢትዮጵያ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን የህብረት ሥራ ማህበራትን ለማጠናከር ያለመ ሪፎርም እያካሄደ ነው። ለዚህም የንቅናቄ ስራን በሁለት ዙሮች በማካሄድ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ብልጽግና በሚያረጋግጥ መልኩ እንዲንቀሳቀሱ ለማድረግ መሰራቱን ገልጸዋል። በዚህ ንቅናቄ መድረኩ የተገኘውን እውቀት ወደ ተግባር በመቀየር በቀበሌ ደረጃ ያሉ ህብረት ሥራ ማህበራት በሪፎርሙ ታግዘው ህብረተሰቡን ይበልጥ ተጠቃሚ የሚያደርጉበትን አቅም ለመገንባት ይሰራል ብለዋል። ንቅናቄው የህብረት ሥራ ማህበራት በሠው ሃይል፣ በፋይናንስና በቴክኖሎጂ የበለጸጉ እንዲሆኑ የሚያግዝ መሆኑን ጠቁመዋል። በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ከ360 በላይ ባለሙያዎች በዚህ በሁለተኛው ዙር የህብረት ሥራ ማህበራት ንቅናቄ መሳተፋቸውንም ተናግረዋል።   በንቅናቄዉ ከተሳተፉ ባለሙያዎች መካከል አቶ ያህያ አህመድ በዚህ ቀበሌ የመድረስ ንቅናቄ ከፍተኛ ልምድ ማግኘታቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚህ የንቅናቄ ስልጠና የህብረት ሥራ ማህበራት ሪፎርም በአግባቡ ለመተግበር የሚያስችለንን እውቀት አግኝተናል ያሉት ደግሞ አቶ ሁሴን አህመድ ናቸዉ።
በድሬዳዋ በግማሽ ቢሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ በተገነቡ ሞዴል ሼዶች አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች የማምረት ስራ ጀምረዋል
Apr 28, 2026 95
ድሬዳዋ፣ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ) በድሬዳዋ በግማሽ ቢሊዮን ብር በሚጠጋ በጀት በተገነቡ ሞዴል ሼዶች አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች የማምረት ስራ መጀመራቸውን የአስተዳደሩ የኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ አስታወቀ። እነዚሁ የአነስተኛና መካከለኛ የኢንዱስትሪ ሼዶች ወደ ማምረት ስራ መግባታቸው፣ የከተማዋን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ከማነቃቃት ባለፈ ለሀገሪቱ የኢንዱስትሪ ሽግግር ትልቅ ፋይዳ እንዳላቸውም ተመላክቷል።   በድሬደዋ አስተዳደር በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የአምራች ኢንዱስትሪዎች ምርትና ምርታማነት መጎልበት እየተከናወኑ የሚገኙት ሁሉንአቀፍ የድጋፍና ክትትል ተግባራት መሠረታዊ ለውጥ በማስገኘት ላይ ናቸው። ጎን ለጎንም አስተዳደሩ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሞዴልነት እየተጠቀሱ የሚገኙ 18 ዘመናዊ የማምረቻ ሼዶችን በመገንባት ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች በማስተላለፍ ውጤታማ ስራ እያከናወነ ይገኛል። የአስተዳደሩ ኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ኡስማን አህመድ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት ከ482 ሚሊዮን ብር በላይ በሚሆን ወጪ 18 ዘመናዊ ሼዶችን ገንብቶ ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች በማስተላለፍ ምርትና ምርታማነት እንዲጨመር አድርጓል። ከ600 እስከ 1ሺህ ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የተገነቡት እነዚሁ ሞዴል ሼዶችን የተረከቡ አነስተኛና መካከለኛ አምራች ኢንዱስትሪዎች አብዛኛዎቹ ወደ ማምረት የተሸጋገሩ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። ጥቂቶቹ ደግሞ የማምረቻ ማሽኖችን ከውጪ በማስገንባት ላይ እንደሚገኙ በማከል። ከድሬዳዋ ኢንዱስትሪ መንደር ጎን ለተገነቡት ሼዶች ሁሉም መሠረተ ልማቶች ከማሟላት ባሻገር አካባቢው ተለይቶ እንዲታጠር መደረጉን አንስተዋል።   ከሼዶቹ በተጨማሪ በጨርቃ ጨርቅ እና አልባሳት ዘርፍ ለተሰማሩ አምራቾችም ባለ አራት ወለል ህንፃ ተገንብቶ ወደ ስራ መገባቱን አስታውሰዋል። እንደ አቶ ኡስማን ገለፃ አነስተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎቹ ከ2ሺህ 800 በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ እድል ከመፍጠራቸው ባሻገር ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በጥራት እና በብዛት በማምረት የውጭ ምንዛሬ እያዳኑ ይገኛሉ። በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት በአስተዳደሩ 490 የአነስተኛና መካከለኛ አዳዲስ አምራች ኢንዱስትሪዎችን ወደ ስራ በማስገባትና ነባሮችን በማጠናከር የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማላቅ በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝም አቶ ኡስማን አስታውቀዋል። "ድሬ ታምርት፤ ኢትዮጵያ ትበልፅግ" በሚል መሪ ቃል በድሬዳዋ የተዘጋጀው የአምራች ኢንዱስትሪዎች ኤክስፖ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት መካሄዱ ይታወሳል።
በአማራ ክልል የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቅንጅት የሚተገበሩ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Apr 28, 2026 107
ባህር ዳር፤ ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በመንግስትና በሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ትብብር የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአማራ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) ገለጹ። የክልሉ ገንዘብ ቢሮ የመንግስትና የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ዓመታዊ የአጋርነት የምክክር መድረክ በባህር ዳር ከተማ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል።   ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ አብዱ ሁሴን (ዶ/ር) በመድረኩ እንደገለጹት፤ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የሚጠበቅባቸውን የልማት አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ምቹ ፖሊሲና አሰራር ተቀርጾ ተግበራዊ ተደርጓል። ድርጅቶቹ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎች፣ በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታና በሰብዓዊ ድጋፍ እያበረከቱ ያለው አስተዋጽኦ የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል።   ድርጅቶቹ ያላቸውን ልምድና ተሞክሮ ተጠቅመው የመንግስትን የልማት አቅጣጫ መሰረት በማድረግ በድህነት ቅነሳና የተለያዩ ችግሮችን በመፍታት የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ተናግረዋል። የማህበረሰብ ድርጅቶቹ በሚያከናውኑት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ላይ ተገቢውን ድጋፍና ጥበቃ እንደሚደረግም አመልክተዋል።   የክልሉ ገንዘብ ቢሮ ኃላፊ አቶ አታላይ ጥላሁን በበኩላቸው፤ በክልሉ በርካታ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በተለያዩ የልማት ዘርፎች እየተሳተፉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ቢሮው የልማት አጋሮች የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡና የሚያጋጥሟቸውን የአሰራር ክፍተቶች እንዲሞላም የአዋጅና የመመሪያ ማሻሻያዎችን እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የምክክር መደረኩ ዋና ዓላማም በመንግስትና በአጋር ድርጅቶች መካከል የአሰራር ግልጸኝነትና ተጠያቂነት በመፍጠር በቅንጅት ለመስራት ያለመ ነው ብለዋል። በቢሮው የሲቪል ልማት ድርጅቶች ማስተባበሪያ ዳይሬክተር አቶ አዝመራው ተጫነ እንዳሉት፤ በክልሉ ያሉ 170 የማህበረሰብ ድርጅቶች ከ24 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት በመመደብ እየሰሩ ይገኛሉ።   በዚህም የክልሉን ማህበረሰብ የሚጠቅሙ የግብርና፣ የጤና፣ የትምህርት፣ የንጹህ መጠጥ ውሃና ሌሎች የልማት ዘርፎች ከ350 በላይ ፕሮጀክቶችን በማከናወን ላይ እንደሚገኙ አብራርተዋል። ለሁለት ቀናት በሚቆየው የምክክርና የልማት ስራዎች ኤግዚቢሽን ማጠናቀቂያ ላይም ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ 25 ድርጅቶች ልዩ እውቅናና ሽልማት እንደሚበረከትላቸው ተመልክቷል።
ያገኘነውን ልምድና እውቀት ተጠቅመን ማህበራት የተሻለ ቁመና ላይ እንዲደርሱ ኃላፊነታችንን እንወጣለን-ሰልጣኞች
Apr 28, 2026 153
ኮምቦልቻ ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ያገኘነውን ልምድና እውቀት ተጠቅመን የሕብረት ሥራ ማህበራት የተሻለ ቁመና ላይ እንዲደርሱ ኃላፊነታችንን እንወጣለን ሲሉ በኮምቦልቻ የሕብረት ስራ ሪፎርም ስልጠና ተሳታፊዎች ገለፁ። የኢትዮጵያ ሕብረት ሥራ ኮሚሽን “ቀበሌ የመድረስ ምዕራፍ” በሚል መሪ ሃሳብ በኮምቦልቻ ሲያካሄድ የቆየው 2ኛው ሀገር አቀፍ የሕብረት ሥራ ሪፎርም የንቅናቄ መድረክና ስልጠና ዛሬ ተጠናቋል።   የስልጠናው ተሳታፊዎች ፤ ከስልጠናው ያገኘነውን እውቀትና ልምድ ተጠቅመን የህብረት ስራ ማህበራት የተሻለ ቁመና ላይ ሆነው ኢኮኖሚውን እንዲያነቃቁ ኃላፊነታችንን እንወጣለን ብለዋል። ከተሳታፊዎቹ መካከል አቶ ሰለሞን እንቁዬ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ኮሚሽኑ የጀመረው ሪፎርም ባለሙያውን በማነቃቃት ገበያውን እያረጋጋ ኢኮኖሚውንም እያሳደገ ይገኛል።   ስልጠናው ህብረት ስራ ማህበራትን ለማጠናከር፣ ለማዘመን፣ የፋይናንስ ስርዓቱን ለማሻሻል፣ የፈጠራ ስራዎችንና አዳዲስ ሀሳቦችን በማዋሀድ በሪፎርሙ የተገኘውን ውጤት ለማስቀጠልና ለማጠናከር ያግዛል ብለዋል። በዚህም ያገኘነውን ልምድና እውቀት ተጠቅመን ማህበራት የተሻለ ቁመና ላይ እንዲደርሱና ኢኮኖሚውን እንዲያነቃቁ የድርሻችንን እንወጣለን ብለዋል። ሌላኛዋ ሰልጣኝ ማርታ ጌቱ በበኩላቸው፣ ስልጠናው የህብረት ስራ ማህበራትን እንቅስቃሴ በማጎልበት ለውጤት እንዲበቃ ሚናው የጎላ መሆኑን አመልክተዋል።   በተለይ ማህበራትን በአዲስ በማደራጀት፣ በቴክኖሎጂ በማስደገፍ፣ ካፒታላቸውን በማሳደግና የቁጠባ ባህላቸውን በማጠናከር ገበያውን እንዲያረጋጉና ኢኮኖሚውን እንዲያነቃቁ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ገልጸዋል። ማህበራት የተሻለ ቁመና ላይ እንዲደርሱ በተከናወኑ ተግባራት የተገኘውን አበረታት ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል በቅንጅት እንሰራለን፣ ለዚህም ከስልጠናው እውቀትና ልምድ አግኝተናል ያሉት ደግሞ አቶ መሀመድ ሆላ ናቸው።   በተለይ ማህበራትን ከሀገር በቀል የኢኮኖሚ ሪፎርም ጋር በማጣጣም የበለጠ ለውጤት እንዲበቁ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመው በኮምቦልቻ ከተማ ተዘዋውረን በመጎብኘት የልምድ ለውውጥም ማድረግ ችለናል ነው ያሉት። የኢትዮጵያ ህብረት ሥራ ኮሚሽን ጽህፈት ቤት ኃላፊና የስልጠናው አስተባባሪ አቶ አምባዬ ወልዴ በበኩላቸው፤ ህብረት ስራ ማህበራትን በማጠናከር፣ በማዘመን፣ ካፒታላቸውን በማሳደግ፣ ትስስር እንዲፈጥሩና የላቀ ደረጃ እንዲደርሱ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡   ለዚህም አዲስ ሪፎርም ተዘጋጅቶ ወደ ትግበራ መገባቱን አስታውሰው ኢኮኖሚውን በማነቃቃትና ገበያውን በማረጋጋት ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸዋል። የበለጠ ለማጠናከርና ባለሙያውንም ለማነቃቃት በተለያየ ዙር ስልጠና እየተሰጠ መሆኑን ጠቁመው በኮምቦልቻ ሲካሄድ የቆየው ስልጠናም ዛሬ መጠናቀቁን ገልጸዋል። ከሚያዚያ 13 ቀን 2018 ዓ/ም ጀምሮ ሲካሄድ በቆየው ስልጠናና የንቅናቄ መድረክ የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና የከተማ አመራሮች እንዲሁም የአማራና የአፋር ክልል የቀበሌ ህብረት ሥራ ማህበራት ባለሙያዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በሀረሪ ክልል በገጠር ኮሪደር ልማት ሁለተኛው ዙር ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ግንባታ ተጀመረ
Apr 28, 2026 82
አዲስ አበባ ፤ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ) ፦ በሀረሪ ክልል በገጠር ኮሪደር ልማት ሁለተኛው ዙር ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ግንባታ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ በተገኙበት ተጀምሯል። ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ሞዴል የአርሶ አደሮች የመኖሪያ መንደር ግንባታ ባስጀመሩበት ወቅት እንዳሉት የክልሉ መንግስት ከመቼውም ጊዜ በላቀ ሁኔታ የዜጎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል። በኮሪደር ልማቱ ሀረር ከተማን ተምሳሌት እንድትሆን ያስቻሉ ውጤታማ ስራዎች እንደተከናወኑ ሁሉ ስኬቱን በገጠር ኮሪደር ልማትም በክልሉ የተለያዩ ወረዳዎች ለመድገም እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።   በክልሉ በተለያዩ ወረዳዎች የሚከናወኑ የገጠር ኮሪደር ልማት ስራዎች አስፈላጊው የመሰረተ ልማት እንዲሟላ ከማድረግ ባለፈ አርሶ አደሩ ዘመናዊና የተመቸ ኑሮ እንዲመራ ያስችላል ሲሉም ተናግረዋል። ከዚህ ቀደምም በገጠር ኮሪደር ልማት የቤት ቁሳቁስ የተሟላላቸው ዘመናዊ የመኖሪያ ቤቶች ተገንብተው ለአርሶ አደሮች እንዲተላለፉ መደረጉን አንስተዋል። በሁለተኛው ዙር ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ፕሮጀክትም 250 ቤቶች እንደሚገነቡ ጠቁመዋል።   ሞዴል የአርሶ አደሮች መንደር ግንባታ አካባቢያዊ ሀብቶችን በመጠቀም እውን እንደሚደረግ ጠቁመው በየአካባቢው የሚገኙ አርሶ አደሮችም ለፕሮጀክቱ መሳካት እንደከዚህ ቀደሙ በቅንጅት እንዲሰሩ ጥሪ አቅርበዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ ከዚህ በተጨማሪም በክልሉ በከተማና በገጠር እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።
በአዊ ብሔረሰብ አሥተዳደር ዞን በመጭው የምርት ዘመን ከ412 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በዘር ይሸፈናል
Apr 28, 2026 94
ባህር ዳር፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በአዊ ብሔረሰብ አሥተዳደር ዞን በመጭው የመኸር ወቅት 412 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በዘር ለመሸፈን እየተሠራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የሰብል ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ አንዱዓለም አያሌው ለኢዜአ እንዳሉት፤ ለመጭው የመኸር ወቅት 412 ሺህ 480 ሔክታር መሬት በዘር በመሸፈን ከ17 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ እየተሠራ ነው።   ከዚህ ውስጥም 70 በመቶው በኩታ ገጠም የሚለማ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅትም ከ85 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት ለ2ኛ ጊዜ ደጋግሞ በማረስ ለዘር ዝግጁ ተደርጓል ብለዋል። ከሚያስፈልገው 840 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ እስካሁን ከ72 በመቶ በላይ የሚሆነውን በማስገባት ለአርሶ አደሩ እየተሰራጨ መሆኑን አረጋግጠዋል። ከ5 ሺህ ኩንታል በላይ የበቆሎ ምርጥ ዘር ተሰራጨቷል ያሉት ቡድን መሪው፤ በመስመር መዝራትና ዘመናዊ ቴክኖሎጅዎችን መጠቀም ላይ በማተኮር እንደሚሰራም አስረድተዋል። በየደረጃው ያለው የግብርና ባለሙያ እና አመራሩ አርሶ አደሩን በመደገፍና በማማከር የሚጠበቀውን የምርት እድገት ለማስመዝገብ በቁርጠኝነት እየሠራ መሆኑን ምአስገንዝበዋል።
በገበታ ለሸገር፣ ለሀገርና ለትውልድ መርሃ ግብሮች የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎች ዘርፉ ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ ይበልጥ የሚያጎሉ ናቸው
Apr 28, 2026 105
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ በገበታ ለሸገር፣ ለሀገርና ለትውልድ መርሃ ግብሮች የተገነቡ የቱሪዝም መዳረሻዎች ዘርፉ ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ ይበልጥ የሚያጎሉ መሆናቸውን የቱሪዝም ሚኒስትር ሠላማዊት ካሳ ገለጹ፡፡ በየአካባቢው የሚገኙ የቱሪዝም ሀብቶችን ለማልማት በቅንጅት እየተሠራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 17ኛ መደበኛ ስብሰባውን አካሂዷል። በምክር ቤቱ የአሠራርና የአባላት ሥነ-ምግባር ደንብ አንቀጽ 92 መሠረት የቱሪዝም ሚኒስትር ሠላማዊት ካሳ በምክር ቤቱ ተገኝተው ከአባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል።   በውይይቱ ላይ አባላቱ በገበታ ለሸገር፣ ለሀገርና ለትውልድ መርሃ ግብሮች የተገነቡ አዳዲስ መዳረሻዎችን በማልማት የቱሪዝም ዲፕሎማሲን እና የኮንፈረንስ ቱሪዝምን ለማጠናከር የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማና አበረታች ናቸው ብለዋል፡፡ እነዚህ ሥራዎች ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአካባቢ ጸጋዎችን ለይተው ወደ ሀብት ለመቀየር ያላቸውን ልዩ ክህሎትና ብቃት የሚያሳዩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ሀገራዊ የቱሪዝም መስህቦችን በመመዝገብ ረገድ እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎችን የሚመለከትም ጥያቄ ቀርቧል። ሚኒስትሯ በሰጡት ማብራሪያ፤ መንግሥት ቱሪዝምን አንዱ የኢኮኖሚ ምሶሶ በማድረግ የመዳረሻ ልማትን ጨምሮ በርካታ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በተለይም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጭነት በገበታ ለሸገር፣ በገበታ ለሀገር እና በገበታ ለትውልድ ፕሮጀክቶች በርካታ የቱሪዝም ስፍራዎችና መዳረሻዎች መገንባታቸውን ጠቅሰዋል። እነዚህ የልማት ሥራዎች ዘርፉ ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ ይበልጥ የሚያጎሉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የመስህብ ምዝገባ ሂደትን በተመለከተም በሰጡት ማብራሪያም አበረታች በሆነ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው እስካሁንም 800 የሚሆኑ የቱሪስት መስህቦች መመዝገባቸውን ይፋ አድርገዋል። በተጨማሪም ሀገር አቀፍ የቱሪዝም ካርታ በማዘጋጀት ረገድ በሲዳማ ክልል የተከናወነው የናሙና ሥራ በስኬት መጠናቀቁን ጠቅሰው ይህንን በመላ ሀገሪቱ የማከናወን ስራ የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ጠቁምዋል፡፡ የግሉ ሴክተር በየአካባቢው የሚገኙ የቱሪዝም ሃብቶችን በማልማት ሂደት ያላቸዉን ተሳትፎ ይበልጥ ለማጎልበት እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ እንዲሁም የማህበረሰቡን አቅም በማስተባበር የማልማት ስራ እና ደረጃቸውን ከፍ የማድረግ ስራዎች እንደሚሰሩም ጠቁመዋል፡፡  
በዞኑ በበጋ መስኖ ተመርተው ለገበያ የቀረቡ ምርቶች ገበያን ማረጋጋት ችለዋል
Apr 28, 2026 99
ጎንደር፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በበጋ የመስኖ ልማት ተመርቶ ለገበያ የቀረበ ከ4 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ገበያውን በማረጋጋት አስተዋጽኦ ማበርከቱን የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለጸ። በመምሪያው የመስኖ ልማት ቡድን መሪ ሀውልቱ ታደሰ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በዞኑ በበጋው ወራቶች ሁሉንም የውሃ አማራጮች በመጠቀም ከ48 ሺህ ሔክታር በላይ በመስኖ ማልማት ተችሏል፡፡   ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር በ15 ሺህ ሔክታር፤ የተገኘው ምርትም በ1 ሚሊየን ኩንታል ብልጫ እንዳለው ተናግረዋል። አርሶ አደሩ ገበያን መሰረት አድርጎ እንዲሠራ በተደረገለት ድጋፍና ክትትል መሰረትም፤ ጤፍ፣ ሩዝ፣ በቆሎ፣ ቲማቲም፣ ሽንኩርት፣ ድንችና ጥቅል ጎመን በማምረት ለገበያ ማቅረብ መቻሉን ገልጸዋል። በአይነትም ሆነ በብዛት ተመርቶ ለገበያ የቀረበው ምርት የገበያ ዋጋን ከማረጋጋቱ ባለፈ፤ ሸማቹ ማህበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ ምርቶቹን እንዲያገኝ አስቻይ ሁኔታ መፍጠር ተችሏል ብለዋል። አርሶ አደሩ ምርታማነትን የሚያሳድጉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችንና አሰራሮችን በስፋት በመጠቀም ለዘመናዊ የመስኖ ልማት መስፋፋት ትኩረት መስጠቱንም ገልጸዋል፡፡ በዚሁ ወቅት ለመስኖ አልሚ አርሶ አደሮች ከ4 ሺህ በላይ የውሃ መሳቢያ ሞተሮችን ጨምሮ ከ50 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በማቅረብ ለመስኖ ልማቱ ድጋፍ መደረጉን አስረድተዋል፡፡ በዞኑ የተገነቡ አነስተኛ፣ መካከለኛና ከፍተኛ የመስኖ አውታሮችም አርሶ አደሩ ከዝናብ ጥገኝነት ተላቆ በዓመት እስከ ሶስት ጊዜ ማምረት የሚችልበትን እድል ፈጥረዋል ነው ያሉት።   አንደኛው ዙር የመስኖ ልማት ተጠናቆ ሁለተኛው ዙር መጀመሩን ጠቁመው በአሁኑ ወቅትም፤ ከ10 ሺህ ሔክታር በላይ መሬት በመስኖ እየለማ እንደሚገኝ አመልክተዋል፡፡
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የኩታ ገጠም የቡና ልማት ውጤት አምጥቷል 
Apr 28, 2026 93
ዲላ፤ ሚያዝያ 20/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በኩታ ገጠም የቡና ልማት የተገኘውን ስኬት ለማስፋፋት እየተሠራ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሠ መሥተዳድር እና የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) ገለጹ። በጌዴኦ ዞን ዲላ ዙሪያ ወረዳ በሽጋዶ ቀበሌ የአረንጓዴ ዐሻራ የቡና ችግኝ ተከላ መርሐ-ግብር ተከናውናል።   አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በአረንጓዴ ዐሻራ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የአፈር ለምነትን በማሻሻል በክልሉ የግብርና ምርታማነት አሳድገዋል። በክልሉ የተጀመረው ቡናን በኩታ ገጠም የማልማት ሥራም በቡና ጥራትና ምርታማነት ላይ ውጤት ማምጣቱን ጠቅሰው፤ ተሞክሮን ለማስፋፋት እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል። ያረጀ የቡና ተክልን በተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች በመተካት ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ፤ ለውጭ ገበያ የሚቀርበውን የቡና መጠን ማሳደግ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። በተያዘው የበልግ ወቅት ከ40 ሚሊየን በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞች ተከላ እየተከናወነ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በምክትል ርዕሠ መሥተዳድር ማዕረግ የግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ናቸው።   ከዚህ ውስጥ ከ5 ነጥብ 6 ሚሊየን የሚልቀው ችግኝ በኩታ ገጠም እንደሚለማ ጠቁመው፤ የቡና ጥራትና ምርታማነትን በማሻሻል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎች ይጠናከራሉ ብለዋል። በተያዘው ዓመት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃሐ-ግብር ቡናና ፍራፍሬን ጨምሮ የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ከ32 ሚሊየን በላይ ችግኞች ተከላ እየተካሄደ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ናቸው። የኩታ ገጠም የቡና ልማትን ለማስፋፋት በተደረገ ጥረት፤ 2 ሺህ 700 አርሶ አደሮችን በማሳተፍ ከ1 ሺህ 200 ሔክታር በላይ መሬት በኩታ ገጠም መልማቱን ገልጸዋል። ዛሬ በዲላ ዙሪያ ወረዳ ሽጋዶ ቀበሌ የተካሄደው የቡና ተከላ መርሐ-ግብርም የዚሁ አካል መሆኑን ተናግረዋል። የሽጋዶ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ዓለማየሁ ገብሬ፤ በአካባቢያቸው እየሰፋ የመጣው የኩታ ገጠም የቡና ልማት ልማዳዊ የቡና ልማትን በማስቀረት ምርታማነት እያሳደገ መሆኑን አንስተዋል። ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በኩታ ገጠም በሚያለሙት መሬት ከ1 ሺህ በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን መትከላቸውንም አስረድተዋል። ከቡና በተጨማሪ በአጭር ጊዜ ውስጥ የሚደርሱ ቦሌቄ፣ እንሰትና ሌሎች ሰብሎችን በመትከል ተጠቃሚ ለመሆን እየሠሩ መሆናቸውንም አመልክተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም