ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ከጋምቤላ ክልል ጋር የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በሌሎች ሰው ተኮር ስራዎች ዙሪያ በትብብር እንሰራለን-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 17, 2026 63
አዲስ አበባ፣ሐምሌ 10/ 2018 (ኢዜአ)፦ ከጋምቤላ ክልል ጋር የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በሌሎች ሰው ተኮር ስራዎች ዙሪያ በትብብር እንሰራለን ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዛሬው ዕለት ከጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወ/ሮ አለሚቱ ኡመድ ጋር በጋራ ለመስራት የሚያስችል ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውን በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል፡፡ በዚህም ወቅት በቀዳማይ ልጅነት እንክብካቤ፣ በኮሪደር ልማት፣ እንዲሁም በሌሎች የሰው ተኮር ስራዎች ዙሪያ እርስ በርስ ልምድ እየተለዋወጥን፣ትብብራችንን አጠናክረን በጋራ ለመስራት ስምምነት ላይ ደርሰናል ብለዋል።
ታላቁ የሕዳሴ ግድብ የቅኝ ግዛት ዘመን የተሳሳተ ትርክትን የሰበረ የፍትሐዊነትና የምክንያታዊነት አህጉራዊ ምልክት ነው - ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም
Jul 17, 2026 65
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ድንበር ተሻጋሪ የውሃ ሀብቶችን በብቸኝነት የመጠቀም የቅኝ ግዛት ዘመን የተሳሳተ ትርክት የሰበረ የፍትሐዊነትና ምክንያታዊነት አህጉራዊ ምልክት መሆኑን በካሊፎርኒያ ስቴት ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስና የሕግ ባለሙያው ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም ገለጹ። ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ገብረማርያም ለኢዜአ እንዳሉት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ መገንባት የቀጣናው ሀገራት የኢኮኖሚ ዕድገትን በማፋጠን ለጋራ ተጠቃሚነት ትልቅ በረከት ከፍቷል። የታችኛው የዓባይ ተፋሰስ ሀገራትም ላይም ሊደስር የሚችለውን የጎርፍ መጥለቅለቅና የውሃ ብክነትን በመቀነስ የተመጣጠነ የውሃ ፍሰት እንዲያገኙ እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የታላቁ ሕዳሴ ግድብን እውን በማድረግ በድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ፍትሐዊ የውሃ ሃብት አጠቃቀም ላይ አዲስ የጋራ ተጠቃሚነት መርህን ማብሰር እንደቻለች ተናግረዋል። ነገር ግን ግብፅ አሁንም ድረስ በዓባይ ወንዝ ላይ ለዘመናት የነበራትን የቅኝ ግዛትና ታሪካዊ በብቸኝነት የመቆጣጠር አባዜ ዛሬም ድረስ እያስተጋባች እንደሚገኝ አስረድተዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በዓባይ ወንዝ ላይ የነበረውን የቅኝ ግዛት ዘመን የተሳሳተ ትርክት በመስበር የጋራ ተጠቃሚነትን ያበሰረ ግዙፍ አፍሪካዊ ፕሮጀክት መሆኑን አንስተዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ የዓባይን ውሃ በብቸኝነት የመጠቀምን የቀድሞ የተሳሳተ አመለካከት መስበሩን የገለጹት ፕሮፌሰር ዓለማየሁ፤ አዲስ የድንበር ተሻጋሪ የውሃ ሃብትን በፍትሐዊና ምክንያታዊነት የመጠቀም አህጉራዊ ምልክት ሆኗል ብለዋል። ግብፅ የቅኝ ግዛት ውሎችን በመጠቀም ለዘመናት የዓባይን ውሃ በብቸኝነት ስትጠቀም መቆየቷን በማስታወስ፤ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ላይ የምታቀርባቸው የተሳሳቱ መረጃዎች መሰረተ ቢስ ክስ መሆኑን ገልጸዋል። እ.ኤ.አ የ1891 የእንግሊዝ ጣሊያን ፕሮቶኮል፣ እ.ኤ.አ የ1906 የብሪታንያ፣ ፈረንሳይና ጣሊያን የሶስትዮሽ፣ እ.ኤ.አ የ1929 የእንግሊዝ ግብፅ እና እ.ኤ.አ በ1959 የግብፅ ሱዳን የተደረጉ ስምምነቶች የዓባይ ምንጭ የሆነችውን ኢትዮጵያ ያገለሉ እንደነበር አስታውሰዋል። የታሪክ ማስረጃን በማጣቀስ በእርግጥ በብቸኝነት የተንቀሳቀሰው ማን ነው? ሲሉ የጠየቁት ፕሮፌሰሩ፤ ኢትዮጵያን ከመክሰስ ይልቅ ከዚህ በፊት የነበሩ ስሁት ትርክቶችን ወደኋላ መመልከት ተገቢ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ በሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ ትብብር መርህ መሆኑን በቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ መድረክ እያስመሰከረች መሆኑን አንስተዋል። የታላቁ ሕዳሴ ግድብም የትብብር እንጂ በብቸኝነት የመጠቀም ፕሮጀክት አይደለም ያሉት ፕሮፌሰር ዓለማየሁ፤ ለዚህም ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ በ2015 ከግብፅና ሱዳን ጋር የፈረመችውን የሕዳሴ ግድብ መርህ ለማክበር በተደጋጋሚ ቃል ገብታለች ብለዋል። የናይል ተፋሰስ የትብብር ማዕቀፍ ስምምነትን የፈረሙት ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ታንዛኒያ፣ ቡሩንዲና ደቡብ ሱዳንም በዓባይ ወንዝ ላይ የቅኝ ግዛት ዘመን አድሏዊ ስምምነቶችን የሻረ መሆኑን አብራርተዋል። እ.ኤ.አ ከ2024 ጥቅምት 13 ጀምሮ በሥራ ላይ የዋለው ማዕቀፍም ፍትሐዊና ምክንያታዊ የውሃ ሃብት አጠቃቀም ሕግ ቢሆንም፤ ግብፅና ሱዳንም ስምምነቱን በመፈረም ትብብርን ሊያጎለብቱ እንደሚገባ አስገንዝዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኖቤል የሰላም ሽልማት ላይ ባደረጉት ንግግር የአፍሪካ ቀንድ የኃያላን መፎካከሪያና የአሸባሪዎች መሸሸጊያ ሳይሆን የሰላም፣ የትብብርና የብልፅግና ቀጣና እንዲሆን ያላቸውን ርዕይ መግለፃቸውን አስታውሰዋል። በሌላ መልኩም እ.ኤ.አ በ2018 በካይሮ ለግብፅ ሕዝብ ኢትዮጵያ የግብፅን የውሃ ጥቅም አትጎዳም በማለት በገቡት ቃል መሰረት የታላቁ ሕዳሴ ግድብ በዓባይ የውሃ ፍስት ላይ አንዳችም ጉዳት እንዳላደረሰ አስረድተዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የጭቅጭቅ መንስኤ ሳይሆን፣ የምስራቅ አፍሪካ የኢኮኖሚ ትስስር፣ የኃይል ትብብርና የጋራ ብልፅግና ማሳለጫ የአፍሪካ ተስፋ መሆኑን አስገንዝበዋል። በተጨማሪም የታላቁ ሕዳሴ ግድብ የአፍሪካ ቀንድና ለመላው አፍሪካ የጋራ ዕድገት ግዙፍ ምልክት ነው ብለዋል።
በሰሜን ሸዋ ዞን ከ199 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የጠጠር መንገዶች ተገንብተዋል
Jul 17, 2026 63
ደብረ ብርሃን ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ199 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ 72 ኪሎ ሜትር የጠጠር መንገድ መገንባቱን የዞኑ መንገድ ትራንስፖርትና ሎጅስቲክ መምሪያ ገለጸ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ደጀኔ በቀለ ለኢዜአ እንደገለጹት፤የተገነቡት አዲስ የጠጠር መንገዶች የመንገድ ተደራሽነት ባልነበረባቸው 11 ወረዳዎች በሚገኙ ቀበሌዎች ውስጥ ነው፡፡ የመንገድ ግንባታው በአገረ ማሪያም ከሰም ወረዳ ቅዱስጌ ከሰም፤በመርሐቤቴ ወረዳ ከዋና መንገድ ሐና ቤተክርስቲያን፤ በሞረትና ጅሩ ዲላሞ ቀበሌን ጨምሮ 11 ወረዳዎች መካሔዱን ጠቅሰዋል፡፡ የተገነቡት መንገዶች ክረምት ከበጋ 42 ሺህ ለሚደርሱ የአካባቢው ነዋሪዎች አገልግሎት መስጠት የሚችሉ መሆኑን ገልፀዋል። የመንገዶቹ መገንባት በዞኑ 3 ሺህ 346 ኪሎሜትር የነበረውን ሽፋን ወደ 3 ሺህ 421 ኪሎሜትር የሚያሳድግ መሆኑን ጠቅሰዋል። በበጀት ዓመቱ ከመንገድ ግንባታው ጎን ለጎን የተለያዩ የድልድይ ግንባታ ስራዎች መከናወናቸውን ነው አቶ ደጀኔ የገለጹት። ለመንገድ ግንባታው ወጪ የተደረገው ከ199 ሚሊየን ብር በላይ የሚሆን ገንዘብ በክልሉ መንግስት የተሸፈነ ሲሆን የማሕበረሰቡ ተሳትፎም ከፍተኛ እንደነበር ገልፀዋል። በመንገድ ዘርፍ በበጀት ዓመቱ ለ7 ሺህ 522 ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ ዕድል መፈጠሩንም አክለው አብራርተዋል፡፡ የተገነቡት መንገዶች የአርሶ አደሩን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትስስር ለማጠናከር የጎላ ድርሻ እንዳላቸው ገልጸዋል።
ባለፉት አምስት ዓመታት አዲስ አበባን የሰላምና የልማት ማዕከል ማድረግ ተችሏል – ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 17, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ ባለፉት አምስት ዓመታት ስር የሰደዱ ችግሮችን በመቅረፍ አዲስ አበባን የሰላምና የልማት ማዕከል ማድረግ መቻሉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2018 በጀት ዓመት ማጠቃለያ የስራ አፈጻጸም ግምገማ ማካሄድ ጀምሯል። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፤ በበጀት ዓመቱ ለመፈጸም የተቀመጡ ግቦች እንዲሁም የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ እቅድ አፈጻጸም እንደሚገመገም ገልጸዋል። ከንቲባዋ ባለፉት አምስት ዓመታት የተያዙ ስትራቴጂክ ግቦችን በተሟላ ሁኔታ በመተግበር በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል። በአዲስ አበባ ስር የሰደዱ ችግሮችን በመፍታትና ስር ነቀል የአስተሳሰብ ለውጥ በመፍጠር ከተማዋን የሰላምና የልማት ማዕከል ማድረግ መቻሉን ጠቁመዋል። አዲስ አበባ ማህበራዊ ፍትህ የነገሰባት፣ ጽዱ፣ አረንጓዴና ውብ ከተማ እንድትሆን የተሰሩ ስራዎች ከተማዋ የዓለምን ትኩረት እንድትስብ ማስቻሉን ጠቅሰዋል። በርካታ ስኬቶች ቢመዘገቡም አሁንም ያልተሻገርናቸው ተግዳሮቶች አሉ ያሉት ከንቲባዋ፣ የአመራሩ የአፈጻጸም ልዩነት እንዲሁም የኑሮ ውድነት ጉዳይ በጥልቀት እንደሚገመገም ተናግረዋል። ከሕዝቡ የመልማት ፍላጎትና ከብልጽግና ግብ አንጻር በርካታ ቀሪ ስራዎች እንዳሉ አመላክተው፣ ስኬቶችን በማስፋት እንዲሁም ተግዳሮቶችን ለይቶ በመፍታት የላቀ አፈጻጸም ለማስመዝገብ መትጋት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
ሀገራዊ የኢኮኖሚ ሽግግርን የሚያረጋግጥ ብቁና ተወዳዳሪ የሰው ኃይል ማፍራት ትኩረት ተሰጥቶታል
Jul 17, 2026 130
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሚያረጋግጥ በዕውቀትና በክህሎት የዳበረ፣ ብቁና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ የሰው ኃይል ማፍራት ቁልፍ ተግባር ተደርጎ እየተሠራበት መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) ገለጹ። የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተሻለ በሬቻ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማጠናከርና የኢንዱስትሪዎችን የሰው ኃይል ፍላጎት ለማሟላት በፖሊሲና በስትራቴጂ ሰፊ የማሻሻያ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው። የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራን በመከተል ዜጎች በቂ የኢንተርፕረነርሺፕ ዕውቀትና ክህሎት ጨብጠው ወደ ሥራ እንዲገቡ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ቀጣይነት ባለው ሁኔታ ሥልጠናዎችን ከገበያ ተጨባጭ ፍላጎት ጋር በማጣጣም ውጤታማ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሚያሳካ፣ ዘመኑን የዋጀ እውቀትና ክህሎት የቀሰመ የሰው ኃይል ማፍራት ልዩ ትኩረት እንደተሰጠውም ጠቁመዋል። ሥልጠናዎች ከንድፈ ሀሳብ ወጥተው በብቃትና በተግባር ላይ የተመሠረቱ እንዲሆኑ ሰፊ የሥርዓተ-ትምህርት ማሻሻያ እየተደረገ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፥ ከአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ጋር ማስተሳሰር ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር መሆኑን ጠቅሰዋል። መንግሥት በክህሎት ልማት ረገድ የጀመረውን ተግባር ይበልጥ ለማጠናከር የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፥ በመላ ሀገሪቱ የግል ዘርፉን ጨምሮ ከ1 ሺህ 500 የቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛ ኮሌጆች መኖራቸውን ተናግረዋል። የማሰልጠኛ ተቋማቱ ከኢንዱስትሪው ፍላጎት ጋር በቀጥታ ትስስር እንዲፈጥሩ እየተደረገ እንደሚገኝም አመላክተዋል። ኢትዮጵያውያን ወጣቶች የፈጣን የቴክኖሎጂ ዕድገት ተጠቃሚና ተዋናይ እንዲሆኑ ለማስቻል ሰፊ የዲጂታል ክህሎት ሥልጠናዎች በሁሉም የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ውስጥ እንዲካተቱ መደረጉን አንስተዋል።
የኮሪደር ልማቱ ባሕርዳር ከተማን በቱሪዝም፣በንግድና ኢንቨስትመንት ተመራጭ አድርጓታል
Jul 17, 2026 103
ባህር ዳር፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ የኮሪደር ልማቱ የባህርዳር ከተማን ውብና ጽዱ በማድረግ በቱሪዝም፣ በንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፎች ተመራጭና ተወዳዳሪ እንድትሆን ማድረጉን የባህርዳር ከተማ አስተዳደር አስታወቀ። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የከተማ አስተዳደሩ ስራ አስኪያጅ አቶ ተሻገር አዳሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የኮሪደር ልማቱ በጣና ሃይቅና አባይ ወንዝ የተከበበችውን ባህርዳር ከተማን ውበት ይበልጥ እንዲጎላ ያደረገ ነው። ከተማ አስተዳደሩ በመጀመሪያውና በሁለተኛው ምእራፍ የኮሪደር ልማት ስምንት ነጥብ ስድስት ኪ.ሜ የሚሆን ስራ ማጠናቀቅ መቻሉን ገልጸዋል። ደረጃቸውን የጠበቁ የሳይክልና የእግረኛ መንገዶች፣ የመንገድ ዳር ማረፊያዎች፣ መብራቶች ፣ፋውንቴኖችና ሌሎች የአረንጓዴ መዝናኛ ስፍራዎችን አካቶ መገንባቱ ከተማዋን ሳቢ እንድትሆን አድርጓታል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም የሶስተኛው ምእራፍ የኮሪደር ግንባታ በመጠናቀቅ ላይ ሲሆን ከተማዋን ይበልጥ ውብና ተመራጭነት ይበልጥ የሚያሳድግ እንደሆነም ነው የገለጹት። ልማቱ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ ለንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፎች ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ የአካባቢውን ኢኮኖሚ ማነቃቃት ያስቻለ መሆኑን አስረድተዋል። በተጨማሪም በከተማዋ ዘመናዊ የአኗኗር ስርዓት ግንባታን በማፋጠን እና የስራ ባህልን በመቀየር ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስገንዝበዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በኮሪደር ልማት ስራው ለ32 ሺህ ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል መፍጠር መቻሉንም ነው ያመለከቱት። ህብረተሰቡም ይዞታውን በነጻ በመልቀቅ፣ በጉልበትና በሀሳብ ካደረገው ተሳትፎ በተጨማሪ ከ500 ሚሊየን ብር በላይ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስገንዝበዋል። የኮሪደር ልማቱ በፈረቃና በቅንጅት በመስራት የስራ ባህልን በመለወጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርከቷል ያሉት ደግሞ የኮሪደር ልማቱ ተቋራጪ ሳይት መሀንዲስ ዳሪክ ተስፋዬ ናቸው። በኮሪደር ልማቱ በቫዞላ ንጣፍ ስራ የተሰማራው ወጣት ምሳው የኋላው በበኩሉ፤ የኮሪደር ልማቱ በከተማዋ እድገትና ዘመናዊነት ላይ የራሴን አሻራ እንዳሳርፍ አድርጎኛል ነው ያለው። ልማቱ በፈጠረላቸው የስራ እድልም ገቢያቸውን በማሳደግ ከራሳቸው አልፎ ሌሎችንም ተጠቃሚ ለማድረግ መቻላቸውን ገልጿል። በክልሉ ዋና ዋና ከተሞች በስፋት እየተካሄደ የሚገኘው የኮሪደር ልማት ስራ የከተሞችን እድገት በማፋጠን በመሰረታዊነት ለውጥ እያመጣ መሆኑ ተመላክቷል።
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን በለውዝ ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ኑሯቸው እየተሻሻለ መምጣቱን ገለጹ
Jul 17, 2026 107
ጭሮ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦በምዕራብ ሐረርጌ ዞን በለውዝ ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች ከዘርፉ በሚያገኙት ገቢ የኑሮ ደረጃቸው እየተሻሻለ መምጣቱን ገልጸዋል። በዞኑ ከዚህ በፊት ከተለመዱት የሰብል ዓይነቶች ባሻገር አርሶ አደሮች በገበያ ተፈላጊ የሆኑ ምርቶችን በስፋት እያመረቱ ሲሆን በተለይም የለውዝ ልማት እየተስፋፋ መምጣቱ ተገልጿል። በዞኑ በተለያዩ ወረዳዎች የሚገኙ አርሶ አደሮችን በለውዝ ልማት ላይ በንቃት በማሳተፍ ገቢያቸውን ይበልጥ እንዲያሳድጉ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም የዞኑ ግብርና እና ተፈጥሮ ሀብት ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። ጽሕፈት ቤቱ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የአመራረት ዘዴዎችን የማሻሻልና የገበያ ትስስር የመፍጠር ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ጠቁሟል። በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የሸነን ዱጎ ወረዳ ልማቱን በኩታ ገጠም እያከናወኑ ያሉ አርሶ አደሮች ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ ከዚህ ቀደም በቆሎና ማሽላ ብቻ ያመርቱበት የነበረውን ማሳ በአሁኑ ወቅት ወደ ለውዝ ልማት በመቀየር ከፍተኛ ገቢ እያገኙ መሆኑን ገልጸዋል። በወረዳው አባድር ቀበሌ የሚኖሩት አርሶ አደር ዲኔ መሐመድ ኡመር እንዳሉት፤ ባለፈው የመኸር ወቅት በለውዝ ካለሙት ሁለት ጥማድ ማሳቸው 10 ኩንታል ምርት አግኝተዋል። ይህንኑ ምርት ለገበያ በማቅረብም ከ100 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘት መቻላቸውን ገልጸዋል። ባገኙት ገቢ የቤት ውስጥ ፍጆታን ከማሟላት ባለፈ፣ ልጆቻቸውን እስከ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ድረስ ከፍለው ለማስተማር እንደረዳቸው ገልጸዋል። ከዚህ ቀደም ማሽላ ብቻ ያመርቱበት የነበረውን አንድ ሄክታር የሚጠጋ ማሳቸውን ካለፉት ሁለት ዓመታት ወዲህ በለውዝ ማልማት መጀመራቸውን የገለጹት ደግሞ ሌላኛዋ የቀበሌው አርሶ አደር ወይዘሮ ሲቲ ከድር ናቸው። ባለፈው መኸር ካለሙት ማሳ 13 ኩንታል ምርት መሰብሰባቸውንና ከዚህም ከ180 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ጠቁመው፤ ባገኙት ገቢም የእርሻ ግብዓቶችን ለማሟላትና እንስሳትን ገዝተው ለማድለብ መቻላቸውን አመልክተዋል። በተመሳሳይ ወጣት ዚያድ አብዱልቃድር እንደተናገረው በአንድ ሄክታር ማሳ ላይ በኩታ ገጠም ካለማው ለውዝ ከ25 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት ማቀዱን ገልጿል። የሸነን ዱጎ ወረዳ እርሻና መሬት ጽሕፈት ቤት የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ አብዮት ውብሸት በበኩላቸው፤ በዘንድሮው የምርት ዘመን በወረዳው ወደ ሦስት ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት በኩታ ገጠም በለውዝ እየለማ መሆኑን አስታውቀዋል። አርሶ አደሮች በመደጋገፍና በመተጋገዝ በልማቱ ተሰማርተው ተጠቃሚነታቸውን እንዲያሳድጉ የዘርፉ ባለሙያዎች የቅርብ ክትትልና ድጋፍ እያደረጉላቸው መሆኑንም ገልጸዋል። በተጨማሪም አርሶ አደሮች ምርታቸውን በተገቢው ወቅት ለገበያ በማቅረብ ተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት እንዲችሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑን ጠቁመዋል። በምዕራብ ሐረርጌ ዞን የሰብል ልማት አስተባባሪ አቶ ሚደቅሳ ደሬሳ በበኩላቸው፤ ዞኑ ለለውዝ ልማት ተስማሚ የአየር ንብረትና የአፈር ጸባይ ያለው በመሆኑ፣ ልማቱ ለአርሶ አደሩ ዋነኛ የገቢ ምንጭ እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል። በተያዘው የመኸር ወቅትም ከ41 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ፣ ከ29 ሺህ 700 ሄክታር በላይ መሬት ላይ ለውዝ በኩታ ገጠም እየለማ መሆኑን ገልጸዋል። ይህ የለውዝ ልማት በዋነኛነት በዞኑ የሸነን ዱጎ፣ ለቡ፣ ቦኬ እና ኦዳ ቡልቱም ወረዳዎች በስፋት እየተካሄደ መሆኑን የጠቀሱት አስተባባሪው፤ ከዚህም ከ700 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል ብለዋል።
የሀረሪ ክልል ምክር ቤት ለ2019 በጀት ዓመት 12 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በጀት አፀደቀ
Jul 17, 2026 114
ሀረር ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ የሀረሪ ክልል ምክር ቤት ለ2019 በጀት አመት 12 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በጀት አፀደቀ፡፡ የክልሉ ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ አመት 10ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ ነው፡፡ ምክር ቤቱ ለሁለት ቀናት እያካሄደ በሚገኘው ጉባኤ ከክልሉ ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ትብብር ቢሮ የቀረበለትን የክልሉን የ2019 በጀት ዓመት 12 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በጀት አጽድቋል። የበጀት ረቂቁን ለምክር ቤቱ ያቀረቡት የክልሉ ፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ትብብር ቢሮ ሃላፊ አቶ መሀመድ ያህያ ናቸው። ከበጀት ድልድሉ ውስጥ ከፍተኛ ድርሻ የሚይዘው የካፒታል በጀት ሲሆን፤ ይህም 65 በመቶ ድርሻ ያለው እንደሆነ ተገልጿል። እንዲሁም 35 በመቶው ለመደበኛ ወጪ ተመድቧል ። በጀቱ የክልሉን የልማት ፍላጎት ለማሳደግ ታሳቢ ተደርጎ የተመደበ መሆኑን ጠቁመው በተለይም በ2018 የበጀት አመት ተጀምረው ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ እንዲሁም በገጠርና በከተማ የሕዝብን የመሰረተ ልማት ጥያቄ ሊመልሱ በሚችሉ ተግባራት ላይ ትኩረት እንደሚሰጥ ተናግረዋል። በተጨማሪም ለገጠር እና ለከተማ ኮሪደር ልማት፣ ለንፁህ መጠጥ ውሃ፣ ለትምህርትና ጤና ሁሉን አቀፍ የልማት ሥራዎች በተሳለጠ መንገድ ለማካሄድ የሚያስችል በጀት መሆኑንም አመልክተዋል። ምክር ቤቱም በቀረበው የ2019 ረቂቅ በጀት አዋጅ ላይ ከተወያየ በኋላ አጽድቋል። በቀጣይም ምክር ቤቱ የተለያዩ ረቂቅ አዋጆች፣እቅዶችና ሹመቶችን ያጸድቃል ተብሎም ይጠበቃል።
በከተማ አስተዳደሩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ተግባራዊ የተደረጉ የልማት ስራዎች ስኬታማ ናቸው
Jul 17, 2026 114
ደሴ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦በከተማ አስተዳደሩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ተግባራዊ የተደረጉ የልማት ስራዎች ስኬታማ መሆናቸውን የደሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሞላልኝ ገለፁ። ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሞላልኝ እንደገለጹት፣ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ሰላምን ከማጽናት ባሻገር ሰፋፊ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎችን ተግባራዊ ለማድረግ ተችሏል። በዚሁ ወቅት ከተከናወኑት የልማት ስራዎች መካከል የኮሪደር ልማትን ጨምሮ የአምስት ኪሎ ሜትር አስፋልት መንገድ ግንባታ ተጠቃሽ መሆኑን አመልክተዋል። በተጨማሪም የትምህርትና የጤና ተቋማትን ደረጃ የማሻሻል እና ሌሎች የማሕበረሰቡን ኢኮኖሚ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ስራዎች ተግባራዊ መደረጋቸውን ተናግረዋል። ከዚሁ ጎን ለጎንም የአገልግሎት አሰጣጥን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መፍታት ተችሏል ያሉት ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው፣ የልማት ስራው በአዲሱ በጀት ዓመትም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በ2019 በጀት ዓመት በተለይ ለመኖሪያ ቤት ግንባታ፣ ለኮሪደር ልማት፣ ገበያን ማረጋጋት፣ ለሥራ እድል ፈጠራና ሌሎችም ሰው ተኮር ፕሮጀክቶች ልዩ ትኩረት እንደሚሰጥ ነው የተናገሩት። የደሴ ከተማ ነዋሪ የሆኑት ሸህ መሀመድ ሰይድ፣ በከተማ አስተዳደሩ በተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። በተለይ በአስፋልት መንገድ ግንባታ፣ በኮሪደር ልማት፣ በገበያ ማረጋጋትና በሌሎችም የተመዘገቡ አበረታች ውጤቶች የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያሳደጉ መሆናቸውን አረጋግጠዋል። የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ አያል ሰይድ በሰጡት አስተያየት፣ የከተማ አስተዳደሩ ነዋሪውን በማስተባበር ሰላም በማጽናት፣ በልማት ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል።
ሞሪሺየስ እና ኢትዮጵያ ትብብራቸውን ማጠናከር የሚችሉባቸው ሰፊ እድሎች አሉ - የሞሪሺየስ ፕሬዝዳንት ድሃራምቢር ጎኩል
Jul 17, 2026 285
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 10/2018(ኢዜአ)፦ ሞሪሺየስ እና ኢትዮጵያ ጤና እና ትምህርትን ጨምሮ የሁለትዮሽ ትስስራቸውን ማጎልበት የሚችሉባቸው አዳዲስ ዘርፎች መኖራቸውን የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ድሃራምቢር ጎኩል ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከሐምሌ 5 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባና በፖርት ሉዊስ መካከል በሳምንት ሦስት ጊዜ የሚደረግ ቀጥታ የመንገደኞች በረራ በይፋ አስጀምሯል። የሞሪሺየስ ፕሬዝዳንት ዳህራምቢር ጎኩል የአየር መንገዱን የቀጥታ በረራ መጀመር አስመልክቶ ለፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ (Pulse of Africa Media POA) እንደገለጹት፤ ጠንካራ የአየር ትስስር የአፍሪካን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት ወሳኝ ነው። አየር መንገዱ ወደ ሞሪሺየስ የጀመረው የቀጥታ በረራ በሀገራቱ መካከል በቱሪዝም፣ በንግድ፣ በኢንቨስትመንትና በሰው ኃይል ልማት ዘርፎች አዳዲስ ዕድሎችን እንደሚፈጥር አመልክተዋል። ጠንካራ የአየር ትስስር የአፍሪካን ሙሉ የኢኮኖሚ አቅም ለመጠቀም ወሳኝ መሆኑን ገልጸው በረራው መጀመሩ የአፍሪካ ህብረት ይበልጥ የተቀናጀች አህጉር ለመፍጠር የሰነቀውን ራዕይ የሚያሳልጥ ነው ብለዋል። ጠንካራ የአየር ትስስር የአፍሪካን ሙሉ የኢኮኖሚ አቅም ለመጠቀም ወሳኝ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል። በአፍሪካ አህጉር ከሚገኙ ታላላቅ ተግዳሮቶች መካከል የትስስር አለመጠናከር ነው ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ ሞሪሺየስን ከኢትዮጵያ ጋር በማገናኘት፣ አፍሪካ ይህንን የቆየ እንቅፋት ለመቅረፍ ተጨባጭ እርምጃዎችን እየወሰደች መሆኑን የሚያሳይ ነው ብለዋል። ይህ አዲስ የበረራ መስመር ከመንገደኞች ማጓጓዝ ባለፈ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የረጅም ጊዜ አጋርነት ለማጠናከር ትልቅ አቅም እንደሆነም አብራርተዋል። ሞሪሺየስ ለዓለም አቀፍ ባለሀብቶችና የንግድ ተቋማት ዋነኛ የአፍሪካ መግቢያ በር ለመሆን እየሰራች መሆኑን ጠቁመውም፤ ይህንን ራዕይ ለማሳካት ጠንካራ የአየር ትስስር መፍጠር ቁልፍ ተግባር ነው ሲሉ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ያለው ሰፊ የአፍሪካና የዓለም አቀፍ የበረራ ተደራሽነት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የንግድና የኢንቨስትመንት ፍሰት በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያሳድገውም ጠቁመዋል። የጭነት ትራንስፖርት (ካርጎ) ከአፍሪካ ዋና ዋና የአቅርቦት ማነቆዎች አንዱ መሆኑን ጠቁመው፣ አዲሱ አጋርነት በአህጉሪቱ ያለውን የዕቃዎች ዝውውር ለማሻሻል ትልቅ ተስፋ እንደሚሰጥ ተናግረዋል። በጋራ መሥራታችን ይህንን የአቅርቦትና የዕቃዎች ዝውውር ችግር ለመፍታት ሰፊ ዕድል ይፈጥርልናል ሲሉም አክለዋል። የኢትዮጵያ የአቪዬሽን ማሰልጠኛ ለሞሪሺየስ ወጣቶች የአውሮፕላን አብራሪነትን ጨምሮ በሌሎች የአቪዬሽን የሙያ ዘርፎች የላቀ የአቅም ግንባታና የስልጠና ዕድሎችን እንደሚከፍት ጠቁመዋል። በቀጣይም በትምህርት፣ በጤና እና በሰማያዊ ኢኮኖሚ (Blue Economy) ዘርፎች ዕውቀትን፣ ቴክኖሎጂንና ልምድን በመለዋወጥ በጋራ ለመሥራት ሰፊ ዕድል እንዳለ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሐምሌ 5 ቀን 2018 ዓ.ም ወደ ሞሪሺየስ በሳምንት ሶስት ቀናት ቀጥታ የመንገደኞች በረራ መጀመሩ ይታወቃል። ይህም መንገደኞች ወደ አፍሪካ፣ አውሮፓ፣ እስያ፣ መካከለኛው ምስራቅ እና አሜሪካ በቀላሉ እንዲጓዙ በማድረግ የአህጉሪቱን ትስስር እንደሚያጠናክር ተመላክቷል።
ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር አሳይታለች
Jul 16, 2026 698
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 9/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ፅኑ ቁርጠኝነት በተግባር ማሳየቷን የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ፀጋ ገለጹ። በኢትዮጵያ የአረንጓዴ አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን ለማጠናከር ለተቀረጸው የምርምር ፕሮጀክት የተዘጋጀ የማስጀመሪያ አውደ ጥናት ተካሂዷል። በአውደ ጥናቱ መክፈቻ የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ፀጋ እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ፅኑ ቁርጠኝነት በተግባር አሳይታለች። ይህም በታዳሽ ኃይል መስፋፋት፣ በዘላቂ ግብርና እና ለአካባቢ ጥበቃ ተስማሚ በሆኑ የኢንዱስትሪ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በግልጽ ይንጸባረቃል ብለዋል። አረንጓዴ ኢኮኖሚን መገንባት የመንግሥትን ጥረት ብቻ ሳይሆን የሁሉንም አካላት ንቁ ተሳትፎ ይጠይቃል ነው ያሉት። በተለይም አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን ማሳተፍ ወሳኝና አማራጭ የሌለው ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። እነዚህ ኢንተርፕራይዞች ለኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለእሴት ሰንሰለት ዕድገት፣ ለሀገር ውስጥ ምርት እንዲሁም ለኢኮኖሚ ብዝኃነት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላቸውም አስገንዝበዋል። ወደ አረንጓዴ ማኑፋክቸሪንግ የሚደረገው ሽግግር የመንግስት፣ የግልና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን የተቀናጀ አካሄድ ይፈልጋል ብለዋል። በኢንስቲትዩቱ በአምራች ዘርፍ የማዕድን ዘርፍ ክፍል ኃላፊ እና መሪ ተመራማሪ ነጻነት ጆቴ (ዶ/ር) በዓለም አቀፍ ደረጃ አካባቢን የማይበክልና ዘላቂ የምርት ሥርዓት መገንባት አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል። በኢትዮጵያ የሚገኙ የአረንጓዴ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን የሚዳስስ ጥናት እንደሚደረግ ጠቁመው የጥናቱ ዋና ዓላማ የኢንተርፕራይዞቹን ወቅታዊ ሁኔታ፣ ዕድሎችንና ፈተናዎችን በማመላከት ተወዳዳሪነታቸውን ማሳደግ ነው ብለዋል። በአፍሪካ ክላይሜት ፋውንዴሽን የፕሮጀክት ማናጀር ሳህሌ ታምሩ ፋውንዴሽኑ በታዳሽ ኃይል፣ አረንጓዴ ኢንዱስትሪ፣ የትራንስፖርትና የፋይናንስ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ጥናቶችና ምርምሮችን እየደገፈ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዘርፍ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም በዓለም አቀፍ ገበያ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ተወዳዳሪነቷንና ተጠቃሚነቷን ለማሳደግ ጥናቱ አስተዋጽኦ የሚያደርግ በመሆኑ በጋራ እንሰራለን ብለዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሞሪሸስ የቀጥታ በረራ አገልግሎት አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያፋጥን ነው
Jul 16, 2026 649
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሞሪሸስ የቀጥታ በረራ አገልግሎት አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያፋጥን መሆኑን የሞሪሸስ ፕሬዝዳንት ዳህራምቢር ጎኩል ገለጹ። የቀጥታ በረራ አገልግሎቱ የቱሪዝም፣ የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የሰው ኃይል ልማት ዕድሎችን የሚያሰፋ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከሐምሌ 5 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባና በፖርት ሉዊስ መካከል በሳምንት ሦስት ጊዜ የሚደረግ ቀጥታ የመንገደኞች በረራ በይፋ አስጀምሯል። የሞሪሺየስ ፕሬዝዳንት ዳህራምቢር ጎኩል የአየር መንገዱን የቀጥታ በረራ መጀመር አስመልክቶ ለፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ (Pulse of Africa Media POA) እንደገለጹት፤ ጠንካራ የአየር ትስስር የአፍሪካን የኢኮኖሚ አቅም ለማጎልበት ወሳኝ ነው። በአዲስ አበባና በፖርት ሉዊስ መካከል የቀጥታ በረራ መጀመሩም፣ የአፍሪካ ኅብረት የአህጉራዊ ኢኮኖሚ ውህደትን የማፋጠን ራዕይ በማሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። ኢትዮጵያም በአቪዬሽን ዘርፍ የአፍሪካን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠን ቁልፍና ተግባራዊ እርምጃ እየወሰደች መሆኗን የሚያሳይ ጠንካራ መልዕክት እንደሚያስተላልፍ ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሞሪሸስ የበረራ አገልግሎትም፣ የሀገራቱን ታሪካዊ ግንኙነት የበለጠ በማጠናከር የኢኮኖሚ ትብብርን እንደሚያጎለብት አንስተዋል። ሞሪሸስ ለዓለም አቀፍ ባለሃብቶችና ለንግድ ተቋማት ወደ አፍሪካ መግቢያ በር ለመሆን እየሠራች በመሆኗ፣ ጠንካራ የአየር ትስስርን ማጎልበት ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካና በዓለም ያለው ሰፊ የበረራ ተደራሽነት፣ በሀገራቱ መካከል የንግድና የኢንቨስትመንት ፍሰትን በእጅጉ በማሳደግ የሎጂስቲክስ ችግሮችን ለመቅረፍ እንደሚያስችል ገልጸዋል። ከአቪዬሽን አገልግሎት ባሻገር፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በፓይለቶችና በሌሎች የአቪዬሽን ባለሙያዎች ስልጠና ያለውን ዓለም አቀፍ ተቀባይነት በመጥቀስ፣ ይህ ለሞሪሸስ ዜጎች ጠቃሚ ዕድል እንደሚፈጥር አስረድተዋል። በቀጣይም በትምህርት፣ በጤና እና በሌሎች ዘርፎች ሀገራቱ በእውቀት፣ በቴክኖሎጂና በልምድ በመለዋወጥ ለሕዝቦቻቸው የጋራ ጥቅም የሚያስገኝ ሰፊ የትብብር አቅም እንዳለ ገልጸዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በበጀት ዓመቱ ከ35 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል
Jul 16, 2026 350
ቡታጅራ ፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተያዘው በጀት ዓመት ከ35 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ገለጸ። የክልሉ ገቢዎች ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት የገቢ ዕቅድ ተግባቦት ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በቡታጅራ ከተማ ተካሂዷል። የቢሮው ኃላፊ ወይዘሮ ቀመሪያ ረሻድ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በክልሉ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ገቢን አሟጦ የመሰብሰብ ሥራው ተጠናክሮ ቀጥሏል። በ2019 በጀት ዓመት የክልሉን ገቢ የማመንጨት አቅምንና የማኅበረሰቡን የልማት ጥያቄ ታሳቢ በማድረግ ከ35 ቢሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ የሚያስችል የገቢ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ተግባር ስለመገባቱም ተናግረዋል። የድጋፍና ክትትል ሥራን በማጠናከር፣ አገልግሎት አሰጣጥን በቴክኖሎጂ በመደገፍ ቀልጣፋ አገልግሎትን ተደራሽ በማድረግ ዕቅዱን ለማሳካት ይሠራል ነው ያሉት፡፡ ከተሳታፊዎች መካከል የስልጤ ዞን የገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ከድር አደም በሰጡት አስተያየት፤ ግብር ለአካባቢው ማኅበረሰብ የልማት ጥያቄ ፈጣን ምላሽ ለመስጠት ያለው ሚና ከፍተኛ ነው። በዞኑ በ2018 በጀት ዓመት የተገኘውን ልምድ በመቀመር በ2019 በጀት ዓመት ከ6 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ መታቀዱንም አመልክተዋል። በልዩ ወረዳው ያለውን የገቢ አማራጭ አሟጦ በመሰብሰብ ወጪን በራስ ገቢ ለመሸፈን ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ እንደሚገኝ የተናገሩት ደግሞ የጠምባሮ ልዩ ወረዳ ገቢዎች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ እንዳሻው አበራ ናቸው። በልዩ ወረዳው እየተመዘገበ ያለውን ዕድገት ለማስቀጠልም በ2019 በጀት ዓመት ከ505 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ መታቀዱን ጠቅሰዋል።
ለእደ-ጥበብ ዘርፍ የተሰጠው ትኩረት በዘርፉ የተሰማሩ ሙያተኞችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደገው ነው
Jul 16, 2026 284
ወልቂጤ፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦በጉራጌ ዞን ለእደ-ጥበብ ዘርፍ የተሰጠው ትኩረት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደገው መምጣቱን በዘርፉ የተሰማሩ ሙያተኞች ገለጹ። የጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ በበኩሉ ዘርፉ ካለው ኢኮኖሚያዊ አበርክቶ ባለፈ የቱሪዝም መስህብን በማሳደግ ረገድ ጉልህ ድርሻ ማበርከቱን አስታውቋል። በዞኑ የባህል አልባሳት፣ የሸክላ ውጤቶችና የቤት መገልገያዎችን ጨምሮ በተለያዩ የእደ-ጥበብ ሥራዎች ላይ የተሰማሩ የአካባቢው አምራቾችና ሻጮች በተሰማሩበት ዘርፍ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። የታንቶስ ባህላዊ እቃዎች ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ወይዘሮ ቅድስት ትዕዛዙ እንዳሉት፣ የጉራጌ ባህል መገለጫ የሆኑ የእደ-ጥበብ ምርቶች ጥራት እንዲጨምር በስልጠናና በተለያየ መንገድ የተደረገላቸው ድጋፍ ሥራቸውን በማሻሻል የተሻለ ገቢ እንዲያገኙ አስችሏቸዋል፡፡ ምርቶቻቸውን እንዲያስተዋውቁ ከተፈጠረላቸው ምቹ ሁኔታ በተጨማሪ በኤግዚቢሽንና በቱሪስቶች መዳረሻ አካባቢዎች የገበያ ቦታ መመቻቸቱ ምርቶቻቸውን ለጎብኚዎች እና ለሸማቾች በቀጥታ እንዲያቀርቡ ማገዙን ተናግረዋል። የጉራጌን ማህበረሰብ ጥበብና ታሪክን የሚያንጸባርቁ የቤት ውስጥ መገልገያዎችንና ጌጣጌጦችን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ሀገር ጎብኚዎች በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መምጣታቸውን ገልጸዋል። የወልቂጤ ማረሚያ ተቋም የእደ ጥበባት ክፍል ተጠሪ አቶ አብድልከሪም ጀማል በበኩላቸው እንዳሉት፤ በተቋሙ የሚከናወነው የእደ ጥበብ ስራ ከቱሪዝም ልማቱ ጋር መተሳሰሩ በኢኮኖሚ በተሻለ ተጠቃሚ አድርጓቸዋል። መንግስት ለእደ-ጥበብ ዘርፉ ድጋፍ ማድረጉ ምርቶቻቸውን በተሻለ ጥራት ለማምረት ከማስቻሉ በተጨማሪ የማህበረሰቡን ታሪክና ባህል በምርቶቻቸው ለማስተዋወቅ እያገዛቸው መሆኑን ተናግረዋል። የጉራጌ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ መሰረት አመርጋ በበኩላቸው፤ የእደ-ጥበብ ዘርፍ የአካባቢውን ባህላዊ እሴት ጠብቆ ለማቆየት እና ለቱሪዝም መነቃቃት ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። ወደ ዞኑ ለሚመጡ ቱሪስቶች የእጅ ሥራዎችን በማቅረብ በዘርፉ ለተሰማሩ ግለሰቦችና ለአካባቢው ተጨማሪ ገቢ እየተገኘ መሆኑን ገልጸው፣ የእጅ ሥራዎቹ የዞኑን በጎ ገጽታ በተሻለ ለማስተዋወቅ ጭምር ያግዛሉ ብለዋል። በዞኑ የዕደጥበብ ምርቶችን ይበልጥ ተወዳዳሪ ለማድረግና ወደላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በስልጠና፣ በፋይናንስ እና በገበያ ትስስር የሚደረጉ ድጋፎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አመልክተዋል።
በክልሉ በበጀት ዓመቱ በገጠርና ከተማ ከ72 ኪሎ ሜትር በላይ የመንገድ መሠረተ ልማት ተገንብቷል
Jul 16, 2026 120
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 9/2018(ኢዜአ)፦ በሀረሪ ክልል በ2018 በጀት ዓመት በገጠርና ከተማ ከ72 ኪሎ ሜትር በላይ የመንገድ መሠረተ ልማት መገንባቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለፁ። ርዕሰ መስተዳድሩ ይህንን የገለፁት እየተካሄደ በሚገኘው የሐረሪ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር 5ኛ ዓመት 10ኛ መደበኛ ጉባዔው ላይ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ሪፖርት ነው። በሪፖርታቸውም በክልሉ በመንገድ መሰረተ ልማት ደህንነትን፤ ፍትሃዊነትንና ተደራሽነትን ለማረጋገጥና የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎትን ለማሻሻል በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተለይም በከተማና በገጠር አዳዲስ የመንገድ መሰረተ ልማት የመገንባትና ነባር የመንገድ መሰረተ ልማት የመጠገን ስራ ሲከናወን ቆይቷል ብለዋል። የመንገድ መሰረተ ልማት ስራዎች ገጠርን ከከተማ እንዲሁም የገጠር ወረዳዎችን የሚያገናኙ መሆናቸውን ጠቁመው በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በክልሉ በገጠርና ከተማ ከ72 ኪሎ ሜትር በላይ የአስፋልትና የጠጠር መንገዶች መገንባታቸውን ነው የተናገሩት። በተጨማሪም በከተማ ከ8 ነጥብ 6 ኪሎ ሜትር በላይ በተለያዩ አካባቢዎች የመንገድ ድሬኔጅ የመገንባትና የመጠገን ስራዎች በትኩረት መከናወናቸውን ርዕሰ መስተደድሩ ጠቁመዋል።
በክልሉ የልማት ዕድሎችን፣ የሰው ኃይልንና እውቀትን አቀናጅቶ በመምራት በየደረጃው ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ ይገባል
Jul 16, 2026 94
አዳማ፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል የልማት ዕድሎችን፣ የሰው ኃይልን እና እውቀትን አቀናጅቶ በመምራት በየደረጃው ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ ይገባል ሲሉ የክልሉ ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። ላለፉት ሦስት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የኦሮሚያ ክልል የ2018 በጀት ዓመት የመንግሥት እና የፓርቲ ሥራዎች ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ተጠናቋል። በመድረኩ ማጠቃለያ ላይ የሥራ አቅጣጫ የሰጡት የክልሉ ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ፣ ከመደመር እሳቤ የተቀዱ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች በፓርቲ፣ በመንግሥት መዋቅርና በተቀናጀ የሕዝብ ተሳትፎ እየተተገበሩ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም በ2018 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ውስጥ በተጨባጭ የታየ መሆኑን ጠቅሰው፣ የተመዘገቡት ድሎች ቀጣይነት እንዲኖራቸው አመራሩ በላቀ ቁርጠኝነት መንቀሳቀስ አለበት ብለዋል። የክልሉ አመራር በሁሉም መስክ ያሉትን የልማት ዕድሎች፣ የሰው ኃይልና ዕውቀትን አቀናጅቶ በመምራት የተጀመረውን የብልጽግና ጉዞ ማጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም የተያዙ ግቦችን ለማሳካት ምቹ የልማት ዕድሎችን መጠቀም እንዲሁም የፋይናንስ አቅምና አማራጮችን ማስፋት ይገባል ብለዋል። በአጠቃላይ የክልሉ አመራር በአዲሱ በጀት ዓመት የልማት ዕድሎችን በሚገባ የሚረዳ፣ ምርታማነትን ለማሳደግ አቅዶ የሚሠራ፣ ቁጠባና ኢንቨስትመንትን የሚያስፋፋ እንዲሁም የሕዝብ እና የአጋር አካላትን ሚና አቀናጅቶ መምራት እንዳለበትም አስረድተዋል። በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ በበኩላቸው፤ የክልሉ አመራር የብልጽግና ጉዞ ግቦችን ለማሳካት የበለጠ መትጋት አለበት ብለዋል። ያለፉት ዓመታት የብልጽግና ጉዞ በብዙ ፈተናዎች የተሞላ ቢሆንም፣ አመራሮቻችንና ፓርቲያችን ታሪክ ለመሥራት አልመው በመንቀሳቀሳቸው ፈተናዎችን ወደ መልካም አጋጣሚ መቀየር ተችሏል ሲሉም አክለዋል። የተገኙ ድሎችን ለማስቀጠል በክልሉ ያለውን ሰፊ የልማት ዕድል እና የሰው ኃይል በቅንጅት በመምራት በሁሉም ረገድ ራስን ለመቻል በሚደረገው ጥረት የላቀ ስኬት ማስመዝገብ እንደሚገባም አሳስበዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን የተሻሻለ የግብርና አሰራር ተግባራዊ መደረጉ ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ ነው
Jul 16, 2026 192
ነገሌ ቦረና፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ቦረና ዞን የተሻሻለ የግብርና አሰራር ተግባራዊ በመደረጉ ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ፡፡ በክልሉ በልግ አብቃይ ከሆኑ አካባቢዎች መካከል አንዱ የሆነው የምስራቅ ቦረና ዞን ከመጋቢት አጋማሽ እስከ ሚያዝያ የበልግ ዝናብና የዘር፣ ከሐምሌ እስከ ነሐሴ አጋማሽ ደግሞ የምርት መሰብሰቢያ ወቅት ነው፡፡ በጽሕፈት ቤቱ የአዝርእት ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ሊበን ቦሩ እንደገለጹት፤ በዞኑ የተሻሻሉ የግብርና አሰራሮችን ተግባራዊ በማድረግ ከለማው ከ176 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ምርት እየተሰበሰበ ነው። በዞኑ በበልግ አዝመራ ከለሙት የሰብል ዓይነቶች መካከል ስንዴ፣ ጤፍ፣ በቆሎና ቦለቄ ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ የበልግ አዝመራውን ምርታማነት ለማሳደግም ከ70 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ ጥቅም ላይ መዋሉንም ገልጸዋል፡፡ በዞኑ የበልግ አዝመራ 162 ሺህ 804 ከፊል አርብቶ አደሮችና አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን ጠቅሰው፣ ይህም የአርብቶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እያገዘ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዞኑ በበልግ አዝመራ ከለማው ሰብልም በ61 ሺህ ሄክታሩ በስንዴ ሰብል የለማ መሆኑንና ከዚህም መሬት 1 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል ብለዋል፡፡ የስንዴ ልማቱን ለማሳደግ የትራክተር፣ የኩታ ገጠምና የመስመር አዘራር ዘዴ እንዲሁም ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ ጥቅም ላይ መዋላቸውን ጠቅሰዋል፡፡ ወጪና ጊዜ በመቆጠብ የምርት አሰባሰብ ሂደቱን ለማፋጠንም ኮምባይነሮች ሥራ ላይ መዋላቸውን አስታውቀዋል፡፡ በዞኑ ሊበን ወረዳ የሜኤሳ ዳሎሬ ቀበሌ ነዋሪ አቶ በዳዳ ጀልዴሳ በአካባቢያቸው የሚስተዋለውን ዝናብ አጠር የአየር ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ እርጥበትን በመጠቀም በዘንድሮ በበልግ አዝመራ 3 ሄክታር መሬት ለመጀመሪያ ጊዜ በተሻሻለ የግብርና አሰራር የስንዴ ምርጥ ዘር ማልማታቸውን ገልጸዋል፡፡ መሬታቸውን በትራክተር አርሰው፣ ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በመጠቀምና ሰብሉን በኮምባይነር እየሰበሰቡ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አቶ አብጉዶ ዋሪዮ፤ በተሻሻለ የግብርና አሰራር ያለሙት ሰብል ውጤታማ እያደረጋቸው እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ መንግስት ለስንዴ ሰብል ልማት የሰጠው ልዩ ትኩረት ለሥራቸው መሳካትና የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥ እንዳገዛቸውም ጠቁመዋል፡፡
በክልሉ ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ ለልማትና ለመልካም አስተዳደር ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል
Jul 16, 2026 245
ቡታጅራ፤ ሐምሌ 9/2018 (ኢዜአ):-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ገቢን በአግባቡ በመሰብሰብ ለህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል። የክልሉ ገቢዎች ቢሮ የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት የገቢ ዕቅድ ተግባቦት ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በቡታጅራ ከተማ እያካሄደ ነው። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ሀላፊ አቶ ስንታየሁ ወልደሚካኤል በዚህ ወቅት እንዳሉት፣ የክልሉን ገቢ በአግባቡ በመሰብሰብ የህዝብን የልማትና የመልካም እስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ የተጀመሩ ሥራዎች ይጠናከራሉ፡፡ በክልሉ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የዘርፉ አመራር ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንዳለበት ጠቅሰዋል፡፡ የገቢ አሰባሰብ ስራውን በልዩ ድጋፍና ክትትል በመምራት በዘርፉ የሚስተዋሉ ብልሹ አሰራሮችን በማረም በክልሉን ፈጣን እድገት ለማረጋገጥ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ ቀመሪያ ረሻድ በበኩላቸው ለክልሉ ህዝብ የልማት ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ገቢን በአግባቡ የመሰብሰብ ስራው በልዩ በትኩረት እየተመራ መሆኑን ተናግረዋል። እንደ ኃላፊዋ ገለጻ በክልሉ በ2018 በጀት ዓመት ከመደበኛና ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት 27 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ 26 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ መሰብሰብ ተችሏል። ገቢው ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ9 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለው ጠቅሰው ለግብር ከፋዩ ማህበረሰብ የተፈጠረው ግንዛቤ፣ የገቢ አሰባሰቡ ወጥ በመደረጉ፣ በቴክኖሎጂ የታገዘ ስራ መሰራቱ እና የድጋፍና ክትትል ስርዓት መጠናከሩ ለገቢው መጨመር አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። በተጀመረው የ2019 በጀት ዓመት 35 ቢሊዮን ብር ገቢ ለማሰባሰብ መታቀዱንና ይህንንም ለማሳካት የግብር ህጉን የማስከበር እና በቴክኖሎጂ የታገዘ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ተደራሽ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ከንጋት ሐይቅ ከ10 ሺህ 700 ቶን በላይ የዓሳ ምርት ተገኝቷል
Jul 16, 2026 186
አሶሳ፤ ሐምሌ 9/2018 (ኢዜአ)፡- ከንጋት ሐይቅ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ10 ሺህ 700 ቶን በላይ የዓሳ ምርት መገኘቱን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ላይ የተፈጠረው ግዙፍ ሰው ሰራሽ ሃይቅ (ንጋት ሃይቅ) የኤሌክትሪክ ሃይል ከማመንጨትና የቱሪስት መስህብ ከመሆን ባለፈ በዓሳ ምርት የስራ እድል መፍጠር ችሏል። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ጉባ ላይ የተንጣለለው የንጋት ሃይቅ ከ70 በላይ ደሴቶች ያሉት ሲሆን በአካባቢው ልዩ ድባብ በመፍጠር ተመራጭ የመዝናኛ ስፍራ የሚሆን ነው። የንጋት ሃይቅ በተለይም ለቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልና አካባቢው ነዋሪዎች ተጨማሪ የኢኮኖሚ መሰረቶችን ይዞ የመጣ አቅም ሆኗል። የንጋት ሐይቅ የዓሣ ሃብት ልማት፣ የቱሪዝምና የውስጥ ለውስጥ የውሃ ትራንስፖርት እንቅስቃሴ እንዲሁም በአካባቢው አዲስ የሥነ-ምህዳርና የአየር ንብረት ሚዛን ለማስጠበቅ የሚያስችል ነው። የክልሉ ግብርና ቢሮ የእንስሳት እና የዓሳ ሀብት ልማት ዘርፍ ምክትል ኃላፊ ብርሃኑ ኢትቻ (ዶ/ር)፤ በንጋት ሐይቅ ዓሳ ማስገር ስራ 46 ማህበራት ተደራጅተው እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከንጋት ሃይቅ ብቻ 1ዐ ሺህ 799 ቶን ዓሳ ማምረት መቻሉን ጠቅሰው በክልሉ የዓሳ ምርት እድገት ማሳያቱን ተናግረዋል። የተገኘው ምርት ከ2017 በጀት ዓመት ጋር ሲነፃፀር በእጥፍ መጨመሩን ገልጸው በቀጣይም ተጨማሪ ማህበራት ወደ ስራ የሚገቡ መሆኑን ጠቁመዋል። በክልሉ ከንጋት ሀይቅ በተጨማሪ ከዳቡስ፣ ዲደሳ እና በለስ ወንዞች የዓሳ ምርት በብዛትና በጥራት መመረቱን አንስተው በተያዘው በጀት ዓመትም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ከክልሉ የዓሳ ምርት ወደ አዲስ አበባ እና ሌሎችም ከተሞች ለገበያ በማቅረብ ሁነኛ የገቢ ምንጭ እየሆነ መምጣቱን ዶ/ር ብርሃኑ ገልጸዋል። የንጋት ሐይቅ በተለይም በዓሳ ምርት ለበርካታ ወጣቶች የስራ እድል እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። በማህበር የተደራጁ ወጣቶች ዓሳ በማስገርና ለገበያ በማቅረብ በሚያገኙት ገቢ ከራሳቸው አልፈው ለቤተሰባቸው ጭምር መትረፋቸውን ገልጸዋል።
በምዕራብ ወለጋ ዞን በበጀት ዓመቱ ለ156 ሺህ ሰዎች ሥራ ተፈጥሯል
Jul 16, 2026 149
ጊምቢ፣ሐምሌ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ወለጋ ዞን በተጠናቀቀው በጀት አመት ለ156 ሺህ ዜጎች የስራ ዕድል መፈጠሩን የዞኑ ሥራ ፈጠራና ክህሎት ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ደረጀ ጉድና ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በበጀት አመቱ ስራ አጥ ወገኖችን በማህበር በማደራጀት ወደ ስራ እንዲገቡ ተደርጓል። በዞኑ በ2018 በጀት ዓመት ለ108 ሺህ ስራ አጥ ወገኖች የስራ ዕድል ለመፍጠር ታቅዶ አፈፃሙን ከፍ በማድረግ ለ156 ሺህ ዜጎች የስራ ዕድል ታጠቃሚ እንዲሆኑ ተደርጓል ብለዋል፡ በዞኑ የስራ አጥነት ችግር ለማቃለል ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት የተከናወኑ ተግባራት አፈፃፀሙን ለማሳደግ እንዳስቻሉ ነው የተናገሩት። የስራ ዕድል የተፈጠረላቸው ወገኖች በግብርና፣ በንግድ፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በእንስሳት ልማት፣በውበት ስራ እና በሌሎች ዘርፎች መሰማራታቸውን ነው የገለጹት። የስራ እድል ለተመቻቸላቸው ዜጎች ከ1 ቢሊዮን ብር ብድር እንዲያገኙ የተደረገ ሲሆን በተሰማሩበት መስክ ዉጤታማ እንዲሆኑም የድጋፍና የክትትል ስራ ሲሰራ ቆይቷል ብለዋል። ከስራ እድሉ ተጠቃሚዎች መካከል መፊዛ አብዲ ከሌሎች ጓደኞቿ ጋር በመሆን ዝሪያቸው የተሻሻሉ በጎችን በማድለብ ስራ ላይ መሰማራታቸውን ነው የምትናገረው። በተሰማሩበት መስክ የተሰጣቸው ሥልጠና፣ ድጋፍ አና ክትትልም ውጤታማ እንዲሆኑ የሚያደርግ በመሆኑ የተሻለ ስኬት ለማስመዝገብ እየሰሩ መሆኑን ነው የገለፀችው። በማኅበር ተደራጅተው የመሥሪያ ቦታና የብድር አገልግሎት ተጠቃሚ በመሆን በዶሮ እርባታ ስራ ላይ መሰማራታቸውን የገለፀው ወጣት እዮብ ቶለሳ በዘርፉ ውጤታማ ስራዎችን እየሰራን ነው ብሏል። በተለይም ከቅርብ አመታት ወዲህ በመንግስት ተቀርጾ ተግባራዊ እየተደረጉ ያሉ የልማት ኢንሼቲቮች ወጣቱ የስራ ዕድል ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን አመልክቷል።