ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
የኮሪደርና የቱሪስት መዳረሻ ልማት ስራዎች ከተሞችን ለኑሮ ምቹ ከማድረግ ባለፈ ዘርፈ ብዙ ዕድሎችን አምጥተዋል
May 5, 2026 143
ሀዋሳ ፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ በከተሞች እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደርና የቱሪስት መዳረሻ ልማት ስራዎች ከተሞችን ለኑሮ ምቹ ከማድረግ ባለፈ ዘርፈ ብዙ ዕድሎችን ይዘው መምጣታቸውን ምሁራን ገለጹ። "በኢትዮጵያ ዘመናዊ ቱሪዝም ልማት ውስጥ ፈጠራና ዘላቂነት" በሚል መሪ ሀሳብ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከኢትዮጵያ ቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 15ኛው ሀገር አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስና የኮሪደር ልማት የልምድ ልውውጥ መድረክ መካሄዱ ይታወሳል። በወቅቱም ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት ምሁራን እንደገለጹት፤ የኮሪደር ልማት የከተሞችን ገጽታ በመቀየር ውብና ማራኪ ከማድረግ ባለፈ የቱሪስት ቆይታን በማራዘም ዘርፈ ብዙ ዕድሎችን ይዞ መጥቷል። በኢትዮጵያ አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደርና የመዳረሻ ልማት ስራዎች የቱሪስትን ቆይታ ከማራዘም ባለፈ ለከተማ ነዋሪው ምቹ የመዝናኛ አማራጭ ይዞ መምጣቱን ነው ምሁራኑ የተናገሩት። በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የስትራቴጂ ፕሮግራሞች ማኔጅመንት ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኢንጂነር እሸታየሁ ክንፉ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ከተሞች ያላቸውን ጸጋ ለይተው የሚያለሟቸው የመዳረሻ ልማት ስራዎች በርካታ ጠቀሜታዎችን ይዘው መጥተዋል። በመላ ሀገሪቱ ከተሞችን ለማዘመንና ምቹ የመኖሪያ፣ የስራና የቱሪስት ማዕከል ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደርና የመዳረሻ ልማት ስራዎች ለነዋሪው ምቹ የመዝናኛ አማራጭና ጎብኚዎች ቆይታቸውን እንዲያራዝሙ ለማድረግ አስችሏል ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ኢኒሼቲቭ አዲስ አበባ ላይ የተከናወኑ የኮሪደርና የመዳረሻ ስፍራዎች ልማት ለዚህ ማሳያ መሆናቸውን ጠቅሰው ይህም የከተማዋን ተመራጭነት በማሳደግ ለገቢ ማደግም የበኩሉን ሚና እየተጫወተ ይገኛል ነው ያሉት። በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዚዳንት ታፈሰ ማቲዮስ (ዶ/ር)፤ በሀዋሳ ከኮሪደር ልማት ስራው በተጓዳኝ የሀይቅ ዳርቻ ልማት ስራውን ዩኒቨርሲቲው በአማካሪነት እያገዘ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የሀይቅ ዳርቻ ልማቱ ደረጃውን የጠበቀ በአካባቢው ያለውን የተፈጥሮ ሀብት ባማከለ መልኩ የሚሰራ በመሆኑ ከተማዋን በአዲስ ገጽታ፣ አዲስ ምዕራፍ ውስጥ እንደከተታት ተናግረዋል። በዩኒቨርሲቲው የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ተባባሪ ፕሮፌሰር ምህረት ደናንቶ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የከተሞችን ውበት የጨመረው የኮሪደር ልማት ስራ የመዝናኛና የገቢ ማግኛም ጭምር ዕድልን ይዞ መምጣቱን ተናግረዋል። የከተማዋ ግርማ ሞገስ የሆነው የሀዋሳ ሀይቅን በተገቢው ለመጠቀም የተጀመረው የሀይቅ ዳርቻ ልማት ስራ ተመራጭነቷን በማሳደግ ለዕድገቷ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ነው ያሉት። የኮሪደርና የመዳረሻ ልማቱ ለቱሪዝም እድገቱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ያመለከቱት ደግሞ በቱሪዝም ማሰልጠኛ ኢንስቲትዩት የከልነሪ አርት ከፍተኛ ኢንስትራክተር አቶ ጌትሽ ገደፋው ናቸው። መንግስት የቱሪዝም ዘርፍ እንዲያንሰራራ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራት ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
በልዩ ኢኮኖሚ ዞኖች የ19 ቢሊዮን ብር ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ ቀርቧል
May 5, 2026 168
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦በልዩ ኢኮኖሚ ዞኖች አማካኝነት በዘጠኝ ወራት ውስጥ 19 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያለው ምርት ለሀገር ውስጥ ገበያ መቅረቡን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን አስታወቀ፡፡ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የአምስት ቢሊዮን ብር ብልጫ የታየበት ሲሆን፣ የተካሄደው ሪፎርምና መንግሥት ያደረገው ድጋፍ ውጤት መሆኑም ተጠቁሟል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) "ኢትዮጵያ ታምርት ለሁለንተናዊ ሉዓላዊነት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል የተዘጋጀውን አራተኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ኤክስፖ በከፈቱበት ወቅት እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ የኢንዱስትሪ ዘርፉ እያደገ መጥቷል። የኢንዱስትሪ ዘርፉ ዕድገት የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ ሲጀመር ከነበረበት 4.7 በመቶ አሁን ላይ ወደ 10.7 በመቶ መድረሱን በወቅቱ ገልጸዋል። ባለፉት አራት ዓመታትም ከውጭ ይገባ የነበረን የ14.5 ቢሊዮን ዶላር ምርት በሀገር ውስጥ መተካት እንደተቻለም ነው የገለጹት። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፍጹም ከተማ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ቀደም ሲል በኢንዱስትሪ ፓርኮች ውስጥ የሚገቡ ኢንቨስተሮች ምርታቸውን 100 በመቶ ለውጭ ገበያ እንዲያቀርቡ የሚገደዱበት አሠራር ነበር። ሆኖም መንግሥት ባደረገው ሪፎርም አምራቾች ምርታቸውን 50 በመቶ ለውጭ፣ 50 በመቶ ደግሞ ለአገር ውስጥ ገበያ እንዲያቀርቡ መፈቀዱን አስታውቀዋል። ይህ አዲስ አቅጣጫ የውጭ ምንዛሬን ከማስገኘት ባለፈ፣ ወደ አገር ውስጥ የሚገቡ ምርቶችን በአገር ውስጥ ምርት ለመተካት (Import Substitution) ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት ብቻ ኮርፖሬሽኑ ከሚያስተዳድራቸው ልዩ ኢኮኖሚ ዞኖች የ19 ቢሊዮን ብር ምርት ለአገር ውስጥ ገበያ መቅረብ መቻሉን አመልክተዋል። አሁን የተገኘው ውጤት የኢንዱስትሪ ፓርኮች ከዓምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከፍተኛ የሆነ ልዩነት ያለው ምርት ለአገር ውስጥ እያቀረቡ መሆኑን እንደሚያሳይ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በርካታ ፋብሪካዎች በግንባታና በማሽን ተከላ ሥራ ላይ የተሰማሩ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፤ እነዚህ ፋብሪካዎች በቅርቡ ወደ ምርት ሲገቡ የአገር ውስጥ ምርት አቅርቦት በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚያድግም አንስተዋል። መንግሥት ያካሄደው ሪፎርምና ኮርፖሬሽኑ ባደረገው ልዩ ድጋፍና ማበረታቻ የተገኘው ውጤት በቀጣይ ዓመታት ይበልጥ እንዲጨምር በትኩረት እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። ኮርፖሬሽኑ የኢንቨስትመንት መዳረሻዎችን በማስፋፋትና ለአምራቾች ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር፣ የአገሪቷን ኢኮኖሚ ለመደገፍ የሚያደርገውን ጥረት አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል።
የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት በሥራ ዕድልና በቴክኖሎጂ ሽግግር ተጠቃሚ አድርጎናል
May 5, 2026 186
ሐረር፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦በሐረሪ ክልል የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት፤ ለዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም ባለፈ የቴክኖሎጂ ሽግግርና ክህሎታቸውን በማሳደግ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው የእድሉ ተጠቃሚዎች ገለጹ። የሐረሪ ክልል በታሪኩና በቱሪስት መስህብነቱ ቢታወቅም፣ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የክልሉን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት በኢንዱስትሪ ልማት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ይገኛል። በተለይም መንግስት የኢንዱስትሪዎችን ምርታማነት ለማሳደግና የውጭ ምንዛሬን ለማዳን የጀመረው "ኢትዮጵያ ታምርት" ንቅናቄ በክልሉ ውጤት ማምጣት ጀምሯል። ክልሉ ለኢንቨስትመንት አመቺ የሆኑ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎችን በማጠናከር፣ አዳዲስ ፋብሪካዎች ወደ ሥራ እንዲገቡና ነባሮቹ ደግሞ በሙሉ አቅማቸው እንዲያመርቱ እያደረገ ያለው ጥረት ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠር ባለፈ፣ የኢንዱስትሪ ባህልና የቴክኖሎጂ ዕውቀት በአካባቢው እንዲሰርጽ እያደረገ ይገኛል። ወጣት ፈርሃን ተውፊቅ የሐረር ከተማ ተወላጅ ሲሆን በከተማው ኢንዱስትሪ ዞን በሚገኘው ማስ ኢንጅነሪንግ ኢንተርፕራይዝ በተለያዩ የሙያ ዘርፍ እርሱና ሌሎች ጓደኞቹ የስራ እድል እንደተፈጠረላቸው ተናግሯል። በክልሉ የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት የተሻለ የቴክኖሎጂ ክህሎት እንዲያገኙ ከማስቻሉ ባለፈ ከውጭ የሚመጡ ምርቶችን በኢንተርፕራይዙ በማምረት የውጭ ምንዛሬን የማስቀረት ተግባር እያከናወኑ መሆኑን አስረድቷል። በከተማው በብረታብረት ዘርፍ ወደ ስራ በመግባት ከኢንዳስትሪው ባገኙት የስራ እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ነስረዲን አህመድ ናቸው። በተለይም የኢንዱስትሪዎች መስፋፋት ለከተማዋ የኮሪደር ልማት የሚውሉ የፖል ብረት ምርቶች በስፋት እንዲቀርቡና ከተማዋን እንዲያስውቡ ማድረጉን አቶ ነስረዲን ገልጸዋል። በዱቄት ፋብሪካ የስራ ዕድል ተጠቃሚ በመሆኗ እራሷንና ቤተሰቧን እያገዘች መሆኑን የገለጸችው ደግሞ ወጣት ኤደን ፍሰሃ ናት። በሐረር የኢንዱስትሪዎች መነቃቃት ለስራ ፈላጊውም ጭምር አስተዋፅኦ እያደረገ መሆኑን ተናግራለች። ከዚህ ባለፈም ልምድ፣ ተሞክሮና የተሻሻሉ አሰራሮችን እየቀሰሙ እንደሚገኙ የገለጸችው ወጣት ኤደን፣ በዚህም ለፋብሪካ ባለቤቶች ምስጋና አቅርባለች። ፋብሪካው 120 ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ፈጥሯል ያሉት ደግሞ በከተማው ኢንዱስትሪ ዞን የሚገኘው የቀነኒ ዱቄት ፋብሪካ ስራ አስኪያጅ አቶ ተስፋ አስፋው ናቸው። ፋብሪካው በአሁኑ ወቅት ከውጪ ይገባ የነበረውን የስንዴ ዱቄት በአገር ውስጥ በማምረት እና ለአካባቢው በማከፋፈል ላይ መሆኑን ጠቁመው፤ በቀጣይም የፓስታ፣ መኮሮኒን እና ሌሎች ምርቶችን ለማምረት የዝግጅት ስራ እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። የሐረሪ ክልል ኢንተርፕራይዞች ልማትና ኢንዱስትሪ ቢሮ ሃላፊ አቶ ኡስማኢል ዩስፍ በበኩላቸው፤ በክልሉ አዳዲስና ነባር መካከለኛና ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎችን ወደ ስራ በማስገባት ተኪ ምርቶችን በስፋት የማምረት ተግባር መጠናከሩን ተናግረዋል። በተለይም የክልሉን ኢኮኖሚ ይበልጥ የሚያጎለብቱና የስራ እድልን የሚያስፋፉ ከፍተኛ ኢንዱስትሪዎች ግንባታቸው ተጠናቆ ማሽነሪዎችን የማስገባት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን አሲዳማ አፈርን በኖራ በማከም ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
May 5, 2026 91
ደብረ ማርቆስ ፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን አሲዳማ አፈርን በኖራ በማከም ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ሃላፊ አቶ ጥላሁን ንጋቱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በመጪው መኸር ምርትና ምርታማነትን በሁሉም አማራጭ በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል ርብርብ እየተደረገ ነው። በዚህም ከ46 ሺህ ሄክታር በላይ በአሲድ የተጠቃ መሬትን በኖራ በማከም ቀድሞ ወደ ነበረበት ምርታማነት ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በኖራ አቅርቦት ዙሪያ ከአቅራቢ ድርጅቶች ጋር በመነጋገር በፍጥነት ለአርሶ አደሩ ለማድረስ እየተሰራ መሆኑን የገለጹ ሲሆን እስካሁን ከ3ሺህ ኩንታል በላይ ኖራ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ተናግረዋል። በቀጣይ ወራትም አስፈላጊውን መጠን ኖራ በማቅረብ አሲዳማ የሆነውን አፈር የማከሙ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። በመኸር ምርቱ የታቀደውን የምርት ጭማሪ ለማስመዝገብም መሬትን በኖራ ከማከም ባሻገር አዳዲስ አሰራሮችንና ቴክኖሎጂዎችን መጠቀም ላይ በማተኮር እየተሰራ ነው ብለዋል። በዞኑ የማቻከል ወረዳ የቅዳማን ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ባየልኝ ሙላት እንደገለጹት በአሲድ የተጠቃውን አንድ ሄክታር ማሳቸውን በኖራ በማከም ዘር እየዘሩ ነው። በኖራ አክመው ከሚዘሩት ሰብል ከአምስት ኩንታል በላይ የምርት ጭማሪ እንዳገኙ ጠቁመው ያገኙትን ጥቅም ለማሳደግም ዘንድሮ ከ30 ኩንታል በላይ ኖራ ማሳቸው ላይ መበተናቸውን ተናግረዋል። በአነደድ ወረዳ የጉዳለማ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ጊዜአለው አግደውም ማሳቸውን በኖራ በማከም ለምነቱ እንዲመለስ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። አሁን ላይም ከግማሽ ሄክታር በላይ ማሳቸው ላይ ኖራ በመበተን ደጋግመው ማረሳቸውን ጠቁመው በቀጣይም ከዘሩ ጋር ቀላቅለው በመዝራት ምርታማነታቸውን ለማሳደግ እንደሚሰሩም አመልክተዋል። በመጪው የመኸር ምርት ከ660 ሺህ ሄክታር በላይ መሬትን በተለያዩ ሰብሎች በማልማት ከ26 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱ ተመልክቷል።
በክልሉ የቡና ኢንሼቲቭ ግቦችን ለማሳካት የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን የማስፋት ሥራ በትኩረት እየተከናወነ ነው
May 5, 2026 101
አዳማ ፣ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ተግባራዊ እየተደረገ ያለውን የቡና ኢንሼቲቭ ግቦችን ለማሳካት፤ የተሻለ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችን የማስፋት ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ሙሐመድሳኒ አሚን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ የቡና ምርታማነትን ለመጨመር የተሻለ ምርት የሚሰጡ ችግኞች ለአርሶ አደሩ በስፋት ተደራሽ እየሆኑ ይገኛሉ። የቡና ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ አንዱ የትኩረት አቅጣጫችን በምርምር የተሻሻሉ የቡና ዝሪያዎችን ለአርሶአደሩ በስፋት ተደራሽ ማድረግ ነው ብለዋል። በክልሉ ለዘንድሮው የቡና ልማት በቂ የቡና ችግኞች ተዘጋጅተዋል ያሉት የቢሮው ምክትል ሃላፊ፤ በአሁኑ ወቅት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የክልሉ ዞኖችና ወረዳዎች የችግኞቹ ተከላ እየተከናወነ ይገኛል ነው ያሉት። በዘንድሮው የቡና ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለመሸፈን ታቅዶ ርብርብ እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። ምርትና ምርታማነትን ለማረጋገጥ የችግኝ ተከላው በሳይንሳዊ ዘዴ እንዲመራ እየተደረገ መሆኑን የገለጹት ምክትል ኃላፊው፤ ለዘርፉ ባለሙያዎችና ለአርሶ አደሮች አስፈላጊው ስልጠና መሰጠቱንም ጠቁመዋል። ምርት የማይሰጡና ያረጁ የቡና ዛፎችን የመንቀልና የተሻለ ምርት በሚሰጡ በአዲስ ዝሪያ የመተካት ስራ ከማከናወን ባለፈ የጉንደላ ስራም በስፋት መከናወኑን ተናግረዋል። በእስካሁኑ ሂደት ያረጀና ተገቢውን ምርት የማይሰጥ ቡና በመንቀል በ66ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተሻለ ምርት የሚሰጡ የቡና ችግኞች መተከላቸውን ተናግረዋል። በተመሳሳይ ባረጀ የቡና ጉንደላ ስራ ከ120ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ያለውን ተክል መሸፈን መቻሉንም ጨምረው ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የቡና ችግኞችን በስፋት ለመትከል የሚያስችል አስተማማኝ የዝናብ ሁኔታ መኖሩን የገለጹት አቶ ሙሐመድሳኒ፤ አርሶ አደሩ በሙሉ አቅሙ ተከላውን በማከናወን ጊዜውን በአግባቡ እንዲጠቀም ተገቢውን ድጋፍና ክትትል እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ በዘንድሮው ዓመት 16 ሚሊዮን ኩንታል የቡና ምርት መሰብሰቡን የገለፁት አቶ ሙሐመሳኒ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 251 ሺህ ቶን ቡና ለማዕከላዊ ገበያ መቅረቡንም ጨምረው ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሀገር ውስጥ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን እያሳደገ ነው
May 4, 2026 141
አዲስ አበባ ፤ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መዋቅራዊ የኢኮኖሚ ሽግግር የሀገር ውስጥ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን እያሳደገ እንደሚገኝ ከፍተኛ የዘርፉ ምሁራንና ተመራማሪዎች ገለጹ። በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል እየተካሄደ የሚገኘው አራተኛው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ዛሬም ቀጥሎ ውሏል። በሁለተኛ ቀን ውሎው በኢትዮጵያ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር፣ በሰው ኃይል ልማትና በምርታማነት አቅም ዙሪያ ያተኮረ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩም የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሲለሺ ለማ፤ ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ዕድገትን የሚያፋጥን ጠንካራ መሰረት እየጣለች ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ጠንካራ መሰረቶችም ምርታማነትና የቴክኖሎጂ ሽግግርን በማፋጠን ዓለም አቀፍ የተወዳዳሪ አቅም እየገነባ መሆኑን ገልጸዋል። የኢንዱስትሪ ምርቶቿንም በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት የትግበራ ሂደት ቀጣናዊ የንግድ ትስስርን አዳዲስ ዕድሎችን እየፈጠረች እንደምትገኝ ተናግረዋል። በተባበሩት መንግስታት የንግድና ልማት ጉባኤ (UNCTAD) የምርታማነት አቅምና ዘላቂ ልማት የአፍሪካ ዲቪዥን ኃላፊ ሙሴ ደለለኝ (ዶ/ር)፤ ኢንዱስትሪ ምርታማነት የዕድገት መሰረት ነው ብለዋል። በዚህም ኢትዮጵያ የፈጠረችውን የኢንቨስትመንት አስቻይ ምኅዳር የበለጠ በማስፋት ዕድገትን የሚያፋጥን የኢንዱስትሪ ምርታማነት ማጠናከር እንደሚጠበቅባት አስገንዝበዋል። በኢትዮጵያ የልማት ምርምር ኢንስቲትዩት የድህነት ቅነሳና ዘርፈ-ብዙ ጥናት ተመራማሪ አለበል ባይራው (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢኮኖሚ መዋቅራዊ ሽግግር የዕድገት ማሳለጫ መሳሪያ ነው ብለዋል። በዚህ በኩል ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ምርታማነትን በማሳደግ ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካት የውጭ ምንዛሬ ወጪን ማስቀረት በሚያስችል ወሳኝ ምዕራፍ እያለፈች መሆኗን ገልጸዋል። በዓለም አቀፍ የዕድገት ማዕከል የኢትዮጵያ ሥራ አስኪያጅ ቴዎድሮስ መኮንን (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለኢንዱስትሪ ምርታማነት አቅም የሆነ የሰው ሃይል ያላት ሀገር ናት ብለዋል። የኢትዮጵያ አብዛኛው ህዝብ በወጣት የዕድሜ ክልል የሚገኝ በመሆኑም የቴክኖሎጂ ሽግግርን ለማፋጠን ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል።
በሀረሪ ክልል ለቱሪዝም ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አበረታች ውጤት የታየበት ነው
May 4, 2026 105
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ በሀረሪ ክልል ለቱሪዝም ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አበረታች ውጤት የተመዘገበበት ነው ሲሉ የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ገለጹ። በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር የተመራው የአስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች የልዑካን ቡድን በሀረር ኢኮ ፓርክ የጅብ ትርኢትን ተመልክተዋል። ከንቲባው በጉብኝታቸው ላይ እንደተናገሩት በክልሉ መሰል የቱሪዝም መስህቦችን ለማስፋፋት የተደረገው ጥረት አበረታች ውጤት የታየበት ነው። በክልሉ የተገነባው የጅብ ትርዒት ማሳያ ፓርክም ለቱሪስቶች ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ያሉት ከንቲባው ይህም የቱሪዝም ዘርፉን በማጎልበት ከተማዋን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ የሚያደርግ መሆኑን ገልፀዋል። የሀረር ከተማን ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎችም ውጤታማና አበረታች መሆናቸውን እንደተመለከቱ ገልጸዋል። በጉብኝቱ ላይ የሀረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪን ጨምሮ የሀረሪ ክልል እና የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ውጤቶችን በማስፋት የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት ማፋጠን ያስፈልጋል
May 4, 2026 105
አዲስ አበባ፣ሚያዚያ 26/2018 (ኢዜአ)፦በሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የተገኙ ውጤቶችን በማስፋት የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዕድገት ማፋጠን እንደሚያስፈልግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የገንዘብ ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማትን የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርት ገምግሟል። የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በሪፖርታቸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በዘንድሮው በጀት ዓመት 10 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት ማስመዝገብ የሚያስችል ስኬት እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። የዋጋ ንረትን ለመቆጣጠር በተሰራው ሥራም በታኅሳስ 2018 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ የዋጋ ግሽበቱን ዘጠኝ ነጥብ ሰባት በመቶ በማድረስ ወደ አንድ አሃዝ ማውረድ መቻሉን አመልክተው፤ የመጋቢት ወርም ወደ ዘጠኝ ነጥብ አራት በመቶ መውረዱን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት መንግስት ከብሔራዊ ባንክ ምንም ዓይነት ብድር አልወሰደም ያሉት ሚኒስትሩ፤ ከብሔራዊ ባንክ ቀጥታ የሚወሰደው ብድር እንዲቆም መደረጉም የዋጋ ንረትን እንዲቀንስ አድርጓል ብለዋል። በቡድን 20 የጋራ ማዕቀፍ አማካኝነት ኢትዮጵያ የዕዳ ሽግሽግ እፎይታ እንድታገኝ ስኬታማ የሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ ድርድር መደረጉን ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብሩ በጥብቅ የፊስካል ፖሊሲ ቁጥጥርና የቁጠባ ዲሲፕሊን በመመራቱ ኢትዮጵያን ከአፍሪካ ቀዳሚ ዕድገት የምታስመዘግብ ሀገር እያደረጋት መሆኑን አንስተዋል። የምክር ቤቱ አባላትም፤ የሚኒስቴሩን የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርት መነሻ በማድረግ በዋጋ ግሽበት፣ የዕዳ ሽግሽግና ተያያዥ የኢኮኖሚ ጉዳዮች ላይ ጥያቄና አስተያየት አቅርበዋል። የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ በምላሻቸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የሚያስከትለውን ጫና ለመቀነስ በደመወዝ ጭማሪ፣ ማዳበሪያ፣ ነዳጅ፣ የምግብ ዘይትና መሰረታዊ ሸቀጦች ላይ መንግስት ድጎማ እያደረገ ነው ብለዋል። በሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ በተደረጉ ስኬታማ ድርድሮችም ኢትዮጵያ ከጣሊያንና ፈረንሳይ ጋር የዕዳ ሽግሽግ ስምምነት መፈረሟን አስረድተዋል። ከቻይና ጋርም የዕዳ ሽግሽግ ስምምነት መፈረም የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው ያሉት የገንዘብ ሚኒስትሩ፤ ከዩሮ ቦንድ አበዳሪዎች ኮሚቴ ጋር ያለው ድርድር መቀጠሉን ገልጸዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ደሳለኝ ወዳጄ፤ ሪፖርቱ ቀጣይነት ያለው ዕድገት መኖሩን የሚያሳይ ነው ብለዋል። በቀጣይም በዋጋ ንረትን፣ ዕዳ ሽግሽግ፣ በወጪና ገቢ ንግድ አፈፃጸም የተገኙ ውጤቶችን በማጠናከር የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርሙን ውጤቶችን በማስፋት ዕድገትን ማስቀጠል እንደሚገባ አሳስበዋል።
ኮርፖሬሽኑ በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ወደ ተግባር ምዕራፍ ተሸጋግሯል
May 4, 2026 133
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ ኮርፖሬሽኑ ባስቀመጠው ራዕይ መሠረት በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ከፍተኛ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቶ አሁን ላይ ወደ ተግባር ምዕራፍ መሸጋገሩን የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዶ/ር ረሻድ ከማል ገለጹ። የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን ጁባ ከተማ በቤት ግንባታ ዘርፍ መሰማራት የሚያስችለውን ታሪካዊ ስምምነት ተፈራርሟል። በሁለቱ ሀገራት መካከል በመሪዎች ደረጃ የጋራ የልማት ትብብር በሚፈልጉ ጉዳዮች ላይ አብሮ ለመስራት ስምምነት መደረሱን ተከትሎ በኮርፖሬሽኑ እና በደቡብ ሱዳን ማዕከላዊ ኢኳቶሪያል ግዛት መካከከል በቤት ልማት ላይ በጋራ መስራት የሚያስችል ስምምነት ተፈጽሟል፡፡ በኢትዮጵያ ፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን እና በደቡብ ሱዳን የማዕከላዊ ኢኳቶሪያል ግዛት መንግሥት መካከል የተደረገው ይህ የመግባቢያ ሰነድ፣ በጁባ ከተማ በቤቶች ልማትና አስተዳደር ዘርፎች በጋራ መሥራት የሚያስችል መሠረት ጥሏል ነው ያለው ኮርፖሬሽኑ። ስምምነቱን የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) እና የማዕከላዊ ኢኳቶሪያ ግዛት መንግሥት አስተዳዳሪ ኢማኑኤል አዲል በይፋ መፈረማቸውን ኢዜአ ከኮርፖሬሽኑ ያገኘው መረጃ ያመላክታል። ይህ ውል ኮርፖሬሽኑ ያለውን የረጅም ጊዜ ልምድና የቴክኒክ አቅም በመጠቀም በጁባ ከተማ ዘመናዊ የመኖሪያ ቤቶች፣ የንግድ ሕንፃዎችና የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ግንባታ እንዲያከናውን ሰፊ መንገድ እንደሚከፍትም ተመላክቷል። ዋና ሥራ አስፈጻሚው በሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደተናገሩት፣ ኮርፖሬሽኑ ባስቀመጠው ራዕይ መሠረት በምሥራቅ አፍሪካና በመላው አህጉሪቱ ገበያዎች ለመሰማራት ከፍተኛ ዝግጅት ሲያደርግ ቆይቶ አሁን ላይ ወደ ተግባር ምዕራፍ ተሸጋግሯል። ኮርፖሬሽኑ ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ያላቸውና አዋጭ በሆኑ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት አድርጎ እየሠራ መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል። በደቡብ ሱዳን የማዕከላዊ ኢኳቶሪያ ግዛት መንግሥት አስተዳዳሪ ኢማኑኤል አዲል በበኩላቸው፣ በኢትዮጵያ እየተመዘገበ ያለው ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና ፈጣን የከተሞች ለውጥ ለመላው አፍሪካውያን ተምሳሌት መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታም በርካታ የልማት ሥራዎችን ተዘዋውረው መመልከታቸውን ተናግረዋል። በተለይም በቤት ልማት ዘርፍ በኢትዮጵያ ያለውን ተሞክሮ ከኮርፖሬሽኑ ጋር በመሆን በጁባ ከተማና በግዛቱ ተግባራዊ ለማድረግ እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል። ስምምነቱ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የኢኮኖሚ ትስስር ከማጠናከር ባሻገር፣ ኮርፖሬሽኑ በቤት አስተዳደርና ልማት ያለውን ውጤታማ ተሞክሮ ለግዛቱ ባለሙያዎች የሚያጋራበትንና የአቅም ግንባታ ሥልጠናዎችን የሚሰጥበትን ዕድል ያመቻቻል ብለዋል። የስምምነቱን አፈጻጸም በቅርበት የሚከታተል፣ ዝርዝር የፕሮጀክት ሰነዶችን የሚያዘጋጅና አጋዥ የመፍትሔ ሐሳቦችን የሚያመነጭ የጋራ ቴክኒክ ኮሚቴ እንዲቋቋም መወሰኑም ተመላክቷል። ይህ ስምምነት የሁለቱ ሀገራት የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ከማሸጋገሩ በላይ፣ የኢትዮጵያን የቤቶች ልማት ተሞክሮ ወደ ጎረቤት ሀገራት ለማስፋፋት ትልቅ መነቃቃትን እንደሚፈጥርም ተገልጿል።
ኢትዮጵያ የቱሪዝም ጸጋዎቿን እንድትጠቀም የግል ዘርፉ የሆቴልና የመዳረሻ ልማት ወሳኝ ነው
May 4, 2026 122
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የቱሪዝም ጸጋዎች በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል የግል ዘርፉ በሆቴልና በመዳረሻ ልማት ላይ የሚኖረው ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባሕር ዳር ታሪኳን ሳትለቅ ዘመኑን እየዋጀች መሆኑን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል። ቀደም ሲል የከተማዋ ትዝታ በነበረው በታሪካዊው ጣና ሆቴል ሥፍራ ዓለም አቀፍ ደረጃን ያሟላ የፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን (Four Points by Sheraton) ሆቴል የግንባታ ፕሮጀክት በይፋ መጀመሩን አመልክተዋል። በሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ የሚገነባው ይህ የሆቴል ፕሮጀክት ከተማዋን የቱሪዝም ሠገነት እንደሚያደርጋት ተናግረዋል። በርካታ አገልግሎቶችን አሟልቶ በአሥራ ስምንት ወራት ግንባታው የሚጠናቀቀው ይህ ሆቴል፣ የግል ባለ ሀብቱ በሀገሪቱ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ ውስጥ ያለውን ሚና በተግባር የሚያሳይ ነው ብለዋል። ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በተለያዩ ዘርፎች እያመጣ ያለው ለውጥ የሚደነቅ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፣ ይህ የሆቴል ግንባታም ለባሕር ዳር በጸጋ ላይ ጸጋ የሚጨምር መሆኑንም ነው የተናገሩት። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ፕሮጀክቱን በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት ለከተማዋና ለሀገሪቱ ሕዝብ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።
በዞኑ ሰላምን በማጽናት የማህበረሰቡን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ይጠናከራሉ
May 4, 2026 111
ደብረ ማርቆስ፣ሚያዚያ 26/2018 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ጎጃም ዞን ሰላምን በማጽናት የማህበረሰቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገለጸ። በዞኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተከናወኑ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ላይ የሚመክር መድረክ በደብረ ማርቆስ ከተማ ተካሄዷል። በመድረኩም የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኑርልኝ ብርሃኑ እንዳሉት፤ በበጀት ዓመቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ሰላምን በማስፈን ለልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ረገድ አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል። በቀሪ ወራትም ተጨማሪ ስራዎችን በማከናወን የበለጠ ስኬት ለማስመዝገብ ርብርብ እንደሚደረግ ጠቅሰው፤ መድረኩም በስራ አፈፃፀም የታዩ ጥንካሬዎችን በማስቀጠል ድክመቶችን ለማረም ታሳቢ ያደረገ ነው ብለዋል። የዞኑ ሰላምና ጸጥታ መምሪያ ሃላፊ አቶ ደምስ አለኸኝ በበኩላቸው፤ በዞኑ የሰፈነው ሰላም የተለያዩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን ለማከናወን ማስቻሉን ጠቁመዋል። በዞኑ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን የማፋጠን ተግባር ህብረተሰቡን ባሳተፈ አግባብ እየተከናወነ ሲሆን ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉም አረጋግጠዋል። በዞኑ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ለተሻሻሉ አሰራሮችና ቴክኖሎጂዎች ትኩረት መሰጠቱን ያነሱት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ ጥላሁን ንጋቱ ናቸው። በዚህም በ2017/18 የምርት ዘመን የሰብል ምርታማነትን በሄክታር ከ35 ወደ 38 ኩንታል ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል። በመኸር ወቅቱ ከለማው ከ640 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ከ23 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰቡን ጠቅሰው፤ በመስኖ ልማቱም እስካሁን ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ተገኝቷል ብለዋል። የአማራ ክልል ምክር ቤት የግብርና፣ የአካባቢ ጥበቃ እና ውሃ ስራዎች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ከፍያለው ሙላቴ፤ በልማትና መልካም አስተዳደር ስራዎች የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት እንዲጠናከሩ አሳስበዋል።
በባህርዳር ከተማ ጸጋን ወደ በረከት የሚቀይሩ ግዙፍ የቱሪዝም ልማት ፕሮጀክቶች እየተገነቡ ነው
May 4, 2026 146
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ በባህርዳር ከተማ የቱሪዝም ጸጋዎችን ወደ በረከት የሚቀይሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች እየተገነቡ እንደሚገኙ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በባህርዳር ከተማ በ3 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር የሚገነባውን ፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና የሆቴል ፕሮጀክት ግንባታን አስጀምረዋል። በታሪካዊው ጣና ሆቴል ባለበት ሥፍራ ላይ በሚድሮክ ኢንቨስትመንት የሚገነባው ይህ ዓለም አቀፍ ሆቴል በ18 ወራት ውስጥ ተገንብቶ እንደሚጠናቀቅ ተገልጿል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት ለባህርዳር ከተማና ለሀገራችን የቱሪዝም መዳረሻነት ከፍታና ለኢኮኖሚ መነቃቃት ትልቅ ብስራት ነው ብለዋል። የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በእርሻ፣ በማዕድንና በሌሎች ዘርፎች የሚያስመዘግበው አስደናቂ ስኬት የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚ ዕድገት የሚያበረክተውን ከፍተኛ ሚና በተግባር የሚያረጋግጥ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የኢንቨስትመንት ግሩፑ በፈታኝ ወቅት ቀድሞ በመገኘትና ክፍተቶችን በመሙላት በኩል የላቀ ተምሳሌትነት መገለጫ እንደሆነም ተናግረዋል። በባህርዳር ግንባታው የተጀመረው ሆቴል ሲጠናቀቅም ጸጋን ወደበረከት በመቀየር ኢትዮጵያ ዘመኑን የዋጀና ዘላቂ ኢኮኖሚ ለመገንባት በጀመረችው ጉዞ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን አንስተዋል። በተለይም በአካባቢው ካሉ የተፈጥሮና ሠው ሠራሽ የቱሪዝም ፀጋዎች ጋር ተዳምሮ ለባህርዳርና ለአካባቢው ዕድገት ትልቅ ዕድል ይዞ እንደሚመጣም አስረድተዋል። መንግሥት የኢትዮጵያና ከተሞቿን የቱሪዝም መዳረሻነት ከፍ የሚያደርጉ ትውልድ ተሻጋሪ ፕሮጀክቶች እንዲሳኩ ለማድረግ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና ሆቴል ፕሮጀክት በፍጥነት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ለማብቃት መትጋት እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል። የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ጀማል አህመድ በበኩላቸው፥ ኩባንያው መንግሥት የፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ለቱሪዝም ዘርፉ መነቃቃት የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ነው ብለዋል። በባህርዳር የሚገነባውን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ሆቴል በ18 ወራት ውስጥ ለማጠናቀቅ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። ሚድሮክ በተለያዩ ከተሞች ለኢትዮጵያ ቱሪዝም ዕድገት ገንቢ ሚና የሚወጡ ዘመናዊ ሆቴሎችን እየገነባ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። በ3 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ወጪ የሚገነባው የፎር ፖይንትስ ባይ ሸራተን ጣና ሆቴል በ32 ሺህ 440 ካሬ ሜትር ላይ የሚያርፍ ሲሆን 120 ዘመናዊ መኝታ ክፍሎችና አራት ዓለም አቀፍ ሬስቶራንቶች፣ ከ1 ሺህ በላይ ሰዎችን ማስተናገድ የሚችል ትልቅ አዳራሽና የመዋኛ ገንዳን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶችን አካቷል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ቀጣናዊ ደኅንነትን ለማስጠበቅ እና ለጋራ ዕድገት ወሳኝ ነው
May 4, 2026 91
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 26/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ለምስራቅ አፍሪካ ቀጣናዊ ትስስር፣ ለጋራ ተጠቃሚነትና ለቀጣናው ደኅንነት መጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ምሁራን ገለጹ። ኢዜአ ያነጋገራቸው ምሁራን እንደገለጹት፤ የሀገሪቱ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ የህልውና እና የቀጣናዊ እድገት ጉዳይ ነው። በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የምጣኔ ሀብት መምህርና ተመራማሪ ዱጋሳ ሙሉጌታ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ ሰላማዊና ዲፕሎማሲያዊ መንገዶችን ተከትላ የባህር በር ለማግኘት የምታደርገው ጥረት የሚበረታታ ነው። የባህር በር ማግኘት የህልውና ጉዳይ መሆኑን አስረድተው፤ ለወጪና ገቢ ንግድ እንቅስቃሴ እንዲሁም ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ፍትሐዊ፣ ሕጋዊ፣ ታሪካዊና መልክዓ-ምድራዊ እውነታን መሰረት ያደረገ መሆኑንም አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ቀጣናዊ ትስስርን በማጎልበት፣ በጋራ ተጠቃሚነት መርህ ላይ የተመሠረተ መሆኑንና ለቀጣናው ሀገራት ዘላቂ ሰላምና የጋራ ልማት የላቀ ጠቀሜታ እንዳለው አስረድተዋል። በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የውሃ ሀብት መምህርና ተመራማሪ ሲሳይ ደመቁ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የባህር በር ከሸቀጥ ዝውውር ባለፈ የሃሳብ፣ የቴክኖሎጂና የቱሪዝም ፍሰትን በማሳለጥ በኩል ያለውን ፋይዳ አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ለምስራቅ አፍሪካ ቀጣናዊ ትስስር፣ ለጠንካራ ደህንነት፣ ለኢኮኖሚና ለቴክኖሎጂ ዕድገት ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑንም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ ማግኘት የሎጂስቲክስ ወጪን በመቀነስ የገቢና ወጪ ንግድ ተወዳዳሪነትን ከማሳደግ ጎን ለጎን፣ ለቀጣናው ደህንነት መጠበቅ ትልቅ ዕድል የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል።
ለኢንቨስትመንት የሚውሉ ሀብቶችን ለማልማት በሚደረገው ጥረት ባለሀብቱ ሚናውን ሊያጠናክር ይገባል
May 4, 2026 74
ባሕር ዳር፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ለኢንቨስትመንት የሚውሉ ሀብቶችን ለይቶ በማልማት ከዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማጎልበት እየተደረገ ባለው ጥረት ባለሀብቱ ሚናውን ሊያጠናክር እንደሚገባ ርዕሠ መሥተዳደር አረጋ ከበደ አሳሰቡ። በባሕር ዳር ከተማ መሬት ወስደው በኢንቨስትመንት ዘርፍ ከተሰማሩ ባለሃብቶች ጋር የውይይት መድረክ ተካሂዷል። ርዕሠ መሥተዳድሩ በዚሁ ወቅት፤ ክልሉ በግብርና፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም እና በሌሎች ዘርፎች የዕምቅ ሃብቶች ባለቤት በመሆኑ ይህን ሀብት በማልማት ክልሉንና ሀገሪቱን የብልፅግና ተምሳሌት ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ባለሃብቱ ሚናውን ሊያጠናክር እንደሚገባ ገልጸዋል። በተለይም በግብርና ዘርፍ ክልሉ ለኤክስፖርትና ለኢንዱስትሪ ግብዓት የሚሆኑ ምርቶች በብዛትና በጥራት የሚመረትበት በመሆኑ ባለሃብቶች በዘርፉ ተሳትፏቸውን እንዲያጠናክሩም ጠይቀዋል ። በማዕድን ዘርፍም የኦፓል፣ የወርቅ፣ የብረት፣ የድንጋይ ከሰልና ለሌሎች አገልግሎት የሚውሉ ሃብቶች ባለቤት በመሆኑ፤ ሃብቱን አልምቶ ለመጠቀም ባለሃብቶች በዘርፉ የበለጠ ሊሳተፉ እንደሚገባም አመልክተዋል። የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው ወደምርት የተሸጋገሩና በግንባታ ላይ የሚገኙ ባለሃብቶች ሥራቸውን በማጠናከር የክልሉን ልማት እንዲያፋጥኑ አሳስበዋል። የክልሉ መንግሥት በዘርፉ የሚስተውሉ የብድር፣ የኤሌክትሪክ አግልግሎትና የመንገድ መሠረተ-ልማት አቅርቦት ክፍተቶችን ለመቅረፍ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራ አረጋግጠዋል። የባሕር ዳር ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው በበኩላቸው፤ አሥተዳደሩ ከተማዋን የቱሪዝምና የኢኮኖሚ ማዕከል ለማድረግ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። በከተማዋ አዲስ ለኢንዱስትሪ መንደር የሚሆን ተጨማሪ 300 ሔክታር መሬት በመለየት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ እስካሁን 122 ሔክታር መሬት ተሸንሽኖ ለባለሀብቶች ዝግጁ መደረጉን አስታውቀዋል። በከተማዋ የኢንቨስትመንት ፈቃድ ወስደው በተለያዩ ምክንያቶች ሥራ ያቆሙ ባለሃብቶች ወደ ሥራ እንዲገቡ መደረጉን ገልፀው፤ ዘንድሮ 23 ፋብሪካዎች ወደማምረት እንዲገቡ መደረጉን አንስተዋል።
የኮሪደር ልማቱ ለቱሪዝምና ኢንቨስትመንት መስፋፋት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
May 4, 2026 132
ባሕር ዳር፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ለቱሪዝምና ኢንቨስትመንት ዘርፉ መስፋፋት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የክልሉ ከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ገለፀ። የቢሮው ኃላፊ ሞላ መልካሙ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ የኮሪደር ልማቱ የተጎሳቆሉ ከተሞችን በማልማት ውበታቸው እንዲወጣ አድርጓል። የከተሞችን የኮንስትራክሽን ዘርፍ ከማነቃቃት ባለፈ ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴያቸው እንዲነቃቃ ማስቻሉንም ጠቁመዋል። ከተሞች ለነዋሪዎች የተመቹ እንዲሆኑ ማድረጉን ገልጸው፤ ለቱሪዝም ዘርፉ ማደግና የከተሞችን የኢንቨስትመንት ፍሰት በማሳለጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም አንስተዋል። በያዝነው ዓመት በ106 ሔክታር ላይ የኮሪደር ልማት ለመሥራት መታቀዱን እና እስካሁን በ80 ሔክታሩ ላይ መከናወኑን አረጋግጠዋል። በዚህ ሥራም የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገድን ጨምሮ 108 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ልማት መከናወኑን አስታውቀዋል። በተሠራው የኮሪደር ልማት 10 የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎች፣ 168 ደረጃቸውን የጠበቁ ካፍቴሪያዎች፣ የሕጻናት መዝናኛዎች፣ የአረጋውያን ማረፊያዎችና ሌሎች ማኅበራዊ አገልግሎት ሰጪ ስፍራዎች መካተታቸውን አብራርተዋል። ለኮሪደር ልማቱ ከ6 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር በላይ ወጪ መደረጉን ገልጸው፤ ከዚህ ውስጥ 3 ነጥብ 4 ቢሊዮኑ ሕብረተሰቡ በገንዘብ፣ በጉልበቱና ቁሳቁስ ተሳትፎ ያደረገበት መሆኑን አስገንዝበዋል። በኮሪደር ልማቱ ለ112 ሺህ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩንም አመላክተዋል። በቀጣይ ልማቱን ወደ ሌሎች ከተሞች የማስፋቱ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው ያመላከቱት።
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በአሲድ የተጠቃ መሬትን በኖራ በማከም የሰብል ምርታማነትን ለማሳድግ እየተሰራ ነው
May 4, 2026 72
ጎንደር፤ሚያዚያ 26/2018(ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በመጪው የመኸር ወቅት ከ12ሺህ ሄክታር በላይ በአሲድ የተጠቃ መሬትን በኖራ በማከም የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ የመምሪያው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ ለኢዜአ እንደገለጹት የሰብል ምርታማነትን ለማሳደግ ከተቀመጡ ስትራቴጂዎች አንዱ አሲዳማ የእርሻ መሬትን በኖራ ማከም ነው፡፡ በዚህም በመኸር ወቅት ሙሉ በሙሉ እና በከፊል በአሲድ ተጠቅተው ምርት መስጠት ያቆሙ የእርሻ መሬቶችን ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ በማከም የሰብል ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በእስካሁኑ ጥረት ከ7 ሺህ ኩንታል በላይ ኖራ በመርጨት 8 ሺህ ሄክታር መሬት ለማከም መቻሉን ገልጸው፣በቀሪ ወራትም ተጨማሪ የእርሻ መሬት ለማከም ሥራው ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል። አቶ ንጉሴ እንዳሉት፥ ካለፉት ዓመታት ተሞክሮ እንደታየው በኖራ ከታከመ መሬት በሄክታር እስከ 15 ኩንታል የምርት ጭማሪ ለማግኘት ተችሏል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ2026 የAPEX መንገደኞች ምርጫ 'በአፍሪካ ምርጡ አየር መንገድ' ሽልማትን አሸንፏል
May 4, 2026 147
አዲስ አበባ፣ሚያዚያ 26/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ2026 የAPEX መንገደኞች ምርጫ 'በአፍሪካ ምርጡ አየር መንገድ' ሽልማትን አሸንፏል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ2026 የAPEX መንገደኞች ምርጫ 'በአፍሪካ ምርጡ አየር መንገድ' (Best Airline in Africa) ሽልማትን በማሸነፍ የአቪዬሽን መሪነቱን አረጋገጠ። ይህ እውቅና አየር መንገዱ በመላው ዓለም በሚያደርጋቸው በረራዎች ቀልጣፋ፣ ምቹ እና አስተማማኝ አገልግሎት ለመስጠት ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ሲሆን፤ ሽልማቱም ሙሉ በሙሉ በመንገደኞች እውነተኛ የጉዞ ተሞክሮ በተሰጠ ድምፅ አማካኝነት ነው። አየር መንገዱ 'ራዕይ 2040' በተሰኘው ስትራቴጂካዊ ዕቅዱ በዓለም ካሉ 20 ቀዳሚ የአቪዬሽን ግሩፖች አንዱ ለመሆን እየሠራ ሲሆን፣ በቶጎ፣ ማላዊ፣ ዛምቢያ እና ኮንጎ ከሚገኙ አየር መንገዶች ጋር በመተባበር የበርካታ ማዕከላት (multi-hub) ስትራቴጂን በመተግበር ላይ እንደሚገኝም ታውቋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ለሀገር ግንባታ የሚፈጥሩ አዕምሮዎችና የሚሠሩ እጆች ዋነኛ ምሰሶዎች ናቸው-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
May 4, 2026 136
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ለሀገር ግንባታ የሚፈጥሩ አዕምሮዎችና የሚሠሩ እጆች ዋነኛ ምሰሶዎች ናቸው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ የሥራና ክህሎት ቢሮ ያዘጋጀው 16ኛው ከተማ አቀፍ የቴክኒክና ሙያ ሳምንት "የቴክኖሎጂ ልህቀት ለሀገር ብልፅግና" በሚል መሪ ሐሳብ በአራዳ ፓርክ ተከፍቷል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች በዚሁ ወቅት፤ በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (Artificial Intelligence) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ኢትዮጵያ በዘርፉ እያሳየች ያለችውን ትልቅ እመርታ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። ሀገር በሚፈጥሩ አዕምሮዎችና በሚሠሩ እጆች ይገነባል ያሉት ከንቲባዋ፤ለዚህም የቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች እያከናወኑ ላለው ተግባር ዕውቅና መስጠት እንደሚገባ ተናግረዋል። ሀገር በልጆቿ ጥረት እንደምትገነባ ገልጸው፤በተለይም በቴክኖሎጂ ዘርፍ እየታየ ያለው ለውጥ ተስፋ ሰጪ መሆኑን ጠቁመዋል። የቴክኒክና ሙያ ዘርፍ ለሀገር የኢኮኖሚ ዕድገትና ለኢንዱስትሪ ሽግግር መሠረት የሚጣልበት መሆኑንም ገልጸዋል። ቀደም ሲል ከውጭ ሀገር በከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ሲገቡ የቆዩ ምርቶች አሁን ላይ በሀገር ውስጥ በቴክኒክና ሙያ ተቋማት መመረት መጀመራቸውን ጠቅሰዋል። በተለይም በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ ግዙፍ የመሠረተ ልማት ሥራዎች የዘርፉ ባለሙያዎች ዕውቀታቸውና ጥበባቸው በተግባር እየታየ መሆኑን ገልጸዋል። ምርቶቹን በሀገር ውስጥ ከመተካት ባለፈ ዓለም አቀፍ ገበያ ላይ ተወዳዳሪ በማድረግ ወደ ውጭ መላክ ላይ ትኩረት ሊደረግ እንደሚገባ አሳስበዋል። ይህ ሂደት ሀገራችን በራሷ አቅም እንድትቆም ትልቅ ማሳያ መሆኑን ገልጸው፤ የከተማ አስተዳደሩ እነዚህን የፈጠራ ሥራዎች ለማስፋፋት የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ኅብረት የሰው ሠራሽ አስተውሎት (AI) እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ (Champion) ሆነው መሾማቸው ይታወቃል። ሹመቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘርፉ ላሳዩት አመራርና ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ የሰው ሠራሽ አስተውሎትንና የፈጠራ ሥራዎችን ለማስፋፋት እየተገበረች ላለው የላቀ ሚና የተሰጠ ዕውቅና መሆኑ በወቅቱ ተገልጿል። ሹመቱ ኢትዮጵያ የሰው ሠራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂን ሥነ ምግባራዊ መርሆች በተከተለ መልኩ በማልማት፣በመመራመር እንዲሁም ተግባራዊ በማድረግ በኩል ከአፍሪካ ቀዳሚዋ ሀገር እንድትሆን ለተሰሩ ሥራዎች ዕውቅና የሰጠ ነው በሚል መገለጹ ይታወሳል።
የግብርና ኢንሼቲቮችን በማስፋት ተረጂነትን ለመቅረፍ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
May 4, 2026 77
ሐረር፤ ሚያዝያ 26/2018 (ኢዜአ)፦ በግብርናው ዘርፍ የተጀመሩ ኢንሼቲቮችን በማስፋትና ምርታማነትን በማሳደግ ሕዝቡን ከተረጂነት የማላቀቅ ሥራ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን የሐረሪ ክልል ምክትል ርዕሠ መሥተዳድር ሮዛ ኡመር ገለጹ። ለእርሻ የሚውል ሁሉንም መሬት በማረስ ምርትና ምርታማነትን የማጎልበት ሥራ ተግባራዊ መደረጉን የገለጹት ወ/ሮ ሮዛ፤ የሚከናወኑ የግብርና ሥራዎችን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ የመስኖ ግድቦች ግንባታ እየተከናወነ ነው ብለዋል። በዚህም መሠረት አርሶ አደሩ የከርሰ ምድር ውኃን የፀሐይ ኃይል በመጠቀም አትክልትና ፍራፍሬ እንዲያለማ መደረጉን ለኢዜአ ተናግረዋል። በሌማት ትሩፋት ዘርፍ የሚገኘውን ምርታማነት ከማሳደግ አኳያም በወረዳዎች ሼዶችን በመገንባት ለወጣቶች እንዲተላለፍ መደረጉን እና ምርጥ ዝርያ ያላቸው የዶሮ ጫጩቶች ለአርሶ አደሩ መሠራጨታቸውን ገልጸዋል። በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ረገድም ሥራዎች በየዓመቱ እያደጉ መምጣታቸውን ጠቅሰው፤ በዘንድሮው በጋ በክልሉ አመርቂ የተፋሰስ ልማት ሥራ መከናወኑን አስታውቀዋል። በዚህም ተረጂ የነበሩ አርሶ አደሮች ምርታማነትን በማጎልበት ከራሳቸው አልፈው ምርታቸውን ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ መልዕክት
May 3, 2026 181
ባሕር ዳር ጥንታዊነትን ከዘመናዊነት። በዚህ አካባቢ ታሪክ መጻፍ ከጀመረ መቶዎች ዓመታት አልፈዋል። ዛሬ ደግሞ ታሪክ ወደፊት እየሄደ ነው። የባሕር ዳር የኢንዱስትሪ፣ የመዝናኛ እና የመሠረተ ልማት ለውጦች ታሪክን ወደ ነገ እየወሰዱት ነው። ዛሬ ከባለ ሀብቶች እና ከአባ ገዳዎች ጋር ሆነን የባሕር ዳርን ስታዲየም፣ አዲሱን የአውሮፕላን ተርሚናል፣ የክልሉን ጠቅላይ ፍርድ ቤት እና የኮሪደር ልማትን ጎብኝተናል። በጉብኝታችን መንገዳችን ትክክል፣ መዳረሻችን አይቀሬ መሆኑን አረጋግጠናል። ባሕር ዳር የሥልጣኔ ዳር ሳትሆን ዕረፍት አይኖረንም።