ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የእንግሊዝ መንግሥት የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን ያደረገው የቴክኖሎጂ ድጋፍ የጋራ ደኅንነትን ለማረጋገጥ ያግዛል
Jun 16, 2026 693
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018(ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ መንግሥት የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን ያደረገው የቴክኖሎጂ ድጋፍ የጋራ ደኅንነትን ለማረጋገጥ እንደሚያግዝ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) ገለጹ። የእንግሊዝ መንግሥት የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን ያደረገው 25 ሚሊየን ብር የሚያወጣ የቴክኖሎጂ እገዛ የርክክብ መርሐ-ግብር እና ጉብኝት በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የአቪዬሽን ደኅንነት ዋና መምሪያ መከናወኑን አገልግሎቱ ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መረጃ አመልክቷል።   በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ዳረን ዌልች የተመራ ልዑክ እንዲሁም የኢትዮጵያ አየር መንገድና የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት መርሐ-ግብር ላይ የአገልግሎቱ ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ድጋፉ በኢትዮጵያና በእንግሊዝ መካከል ያለውን ትብብርና የጋራ ደኅንነትን የማረጋገጥ አጋርነት ማሳያ ነው። መርሐ-ግብሩ በኢትዮጵያና በእንግሊዝ መካከል ያለውን ዘላቂ አጋርነት የሚያሳይ ወሳኝ ምዕራፍ መሆኑን ጠቁመው፤ የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን የተደረገው የቴክኖሎጂ ድጋፍ በትብብር ስንሰራ በጋራ ደኅንነትና በዓለም አቀፍ ትስስር አውድ የምናሳካቸውን ድሎች ያሳያል ብለዋል። የአቪዬሽን ደኅንነት ስጋት ተለዋዋጭና በየጊዜው እያደገ የሚመጣ የዘርፉ ፈተና ነው። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ ያለውን የበላይነት አስጠብቆ ለመዝለቅ የደኅንነት ስጋቶችን አስቀድሞ በማወቅ ማስቀረት ወሳኝ ተልዕኳች ነው ያሉት ዶ/ር ሲሳይ፤ የቴክኖሎጂ ድጋፉ የመፈጸም አቅምን ያሳድጋል ሲሉ ተናግረዋል።   ኢትዮጵያና እንግሊዝ ትብብራቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቁመው፤ በተለይ በቢሾፍቱ የሚገነባው አዲሱ የአየር ማረፊያና ሀገሪቱ እ.አ.አ በ2027 የምታስተናግደው የኮፕ-32 ጉባኤ በተለያዩ የአጋርነት ማዕቀፎች የሚገለጹ ወሳኝ ሁነቶች መሆናቸውን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በዓመት እስከ 120 ሚልየን መንገደኞችን የሚያስተናግድ በአፍሪካ ግዙፍ የሆነ አየር ማረፊያ እየገነባች መሆኑን አመልክተው፤ ይህ ከአቪዬሽን ደኅንነት አኳያ ከፍተኛ ዝግጁነት እንደሚፈልግ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ዳረን ዌልች በበኩላቸው፤ ሁለቱ ሀገራት እስከ ዛሬ የዘለቀና ጠንካራ ወዳጅነት እንዳላቸው ጠቁመዋል። የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን የተደረገው እገዛ ይህንኑ የሚመሰክርና የሚያጠናክር መሆኑንም አመልክተው ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ደኅንነት ዘርፍ ያላት ቁመና የሚደነቅ መሆኑንም መስክረዋል። በየእለቱ የምታከናውኑት ተግባር የሀገሪቱንም የእኛንም ደኅንነት ስለሚያረጋግጥ አድናቆቴን መግለጽ እወዳለሁ ያሉት አምባሳደሩ የቦሌ ዓለም-አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ቁልፍ የሆነ የዓለም-አቀፍ ተጓዞች መዳረሻና ማዕከል ነው፡፡ ደኅንነትን የማረጋገጥ ጉዳይ የሁላችንም የጋራ ኃላፊነት መሆኑ ይታወቃል ብለዋል።   በዓለም አቀፍ ደረጃ እየተከሰቱ ያሉ የበረራ ደኅንነት ስጋቶችን ለመቀነስ ዘመናዊ መሣሪያዎችን መታጠቅ መፍትሔ ስለሚሆን በአፍሪካ ለመጀመሪያ ጊዜ ስራ ላይ የሚውል ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ለኢትዮጵያ መበርከቱንም ተናግረዋል። የአቪዬሽን ደኅንነት ዋና መምሪያ ዳይሬክተር አስራት ቀጄላ፤ ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ደኅንነት ዘርፍ ዓለም-አቀፍ መመዘኛዎችን በብቃት በማሟላት ተጠቃሽ ሀገር መሆኗን አረጋግጠዋል። የእንግሊዝ መንግሥት ድጋፍም በተለያየ መንገድ ሲገለጽ መቆየቱን አመልክተው፤ ለተደረገው እገዛም ምስጋና አቅርበዋል። ከእንግሊዝ መንግሥት ጋር በተለያዩ የተቋማዊ ግንባታ መስኮች ዘርፈ ብዙ ትብብሮችን ስናደርግ ቆይተናል ይህም ለኢቪዬሽንና ለዓለም-አቀፍ አየር ትራንስፖርት ዘርፍ ደኅንነት መረጋገጥ ጉልህ ሚና ወደ ሚያበረክት ስትራቴጂክ ምዕራፍ ተሸጋግሯል ሲሉም ገልጸዋል። የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን የተደረገው ድጋፍ ዘመኑን የዋጀ የበረራ ደኅንነትን ለማከናወን ከፍተኛ ሚና እንደሚያበረክት አቶ አስራት አመልክተዋል። በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ በኩል የተደረገው ድጋፍ ከሀገሪቱ ‹‹ሆም ኦፊስ ኢንተርናሽናል ኦፕሬሽን›› ቢሮ የተገኘ መሆኑን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለመገናኛ ብዙኃን የላከው መረጃ ጠቁሟል።
የቱሪዝም ዘርፉን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ለማዘመን እየተሰራ ነው
Jun 16, 2026 238
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዲጂታል ቴክኖሎጂ አማራጮችን በመጠቀም የቱሪዝም ዘርፉን ለማዘመን እየሰራች መሆኑን የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስትር ዴኤታው ከዓለም አቀፉ የብራንዲንግ እና ሚዲያ ተቋም "FAME by Sheeraz" መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ ሺራዝ ሀሰን እና የልዑካን ቡድናቸው ጋር በቱሪዝም ዘርፍ በትብብር መስራት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል። እንደገና አበበ (ዶ/ር) መንግስት ባለፉት ስምንት ዓመታት አዳዲስ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በመገንባት፣ ነባሮቹን በማደስ እና የዲጂታል ቴክኖሎጂን (Visit Ethiopia Portal) በመጠቀም ዘርፉን ለማዘመን እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም አዲስ አበባን የአህጉሪቱ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ እየተደረገ ያለውን ጥረት ጠቅሰው፤ እንደ "FAME by Sheeraz" ባሉ ተቋማት አማካኝነት የኢትዮጵያን የቱሪዝም ሀብቶች በዓለም አቀፍ ደረጃ ማስተዋወቅ አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል። የ"FAME by Sheeraz" መስራች ሺራዝ ሀሰን በበኩላቸው፣ ድርጅታቸው በአሜሪካ፣ በአውሮፓ እና በመካከለኛው ምስራቅ ታዋቂ ግለሰቦችን እና የንግድ ምልክቶችን በማስተሳሰር የረጅም ጊዜ ልምድ እንዳለው ገልጸዋል። ይህንን ልምድ በመጠቀም የኢትዮጵያን ገጽታ ለመገንባት በጋራ ለመስራት ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው የገለጹት ዋና ስራ አስኪያጁ፤ ለተግባራዊነቱም ተቋሙ በአዲስ አበባ ቋሚ ጽሕፈት ቤት እንደሚከፍት ጠቁመዋል። በተጨማሪም በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) የታገዙ የመገናኛ ብዙኃን አማራጮችን በመጠቀም ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ ስትራቴጂያዊ እቅድ ቀርጸው ለመንቀሳቀስ ዝግጁ መሆናቸውን ነው ዋና ስራ አስኪያጁ ያረጋገጡት። በውይይቱ ወቅት፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል የተነሱትን ነጥቦች ወደ ተግባር ለመቀየር ስምምነት ላይ መደረሱን የቱሪዝም ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
የከተማዋ እድገት ተደማሪና ቀጣይነት ያለው እንዲሆን አመራሩ በቁርጠኝነትና በተደራጀ መንገድ ሊመራ ይገባል
Jun 16, 2026 712
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-የአዲስ አበባ ከተማ እድገት ሁልጊዜም ተደማሪና ቀጣይነት ያለው እንዲሆን አመራሩ በቁርጠኝነትና በተደራጀ መንገድ ሊመራ እንደሚገባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ በቀጣዮቹ 90 ቀናት መሪ ዕቅድ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ አካሂዷል።   የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ ባለፉት ጊዜያት የተመዘገቡ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠልና በከተማዋ የተጀመሩ ግዙፍ የልማትና የሪፎርም ሥራዎችን በላቀ ፍጥነት ለማጠናቀቅ የ90 ቀናት መሪ ዕቅዱ ሚና የጎላ ነው ብለዋል። ዕቅዱ በዋናነት የሕዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ፣ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መፍታት፣ አገልግሎት የማሻሻል ስራን በማጠናከር የመሶብ አንድ ማእከል ዲጂታል አገልግሎትን ማስፋት፣ የኑሮ ውድነትን ማረጋጋት፣ የንግድ ስርዓቱን መግራት፣ የስራ እድል ፈጠራ እና የወጣቶችና ሴቶች ተጠቃሚነት ላይ መስራት ነው ብለዋል። እንዲሁም የአረንጓዴ አሻራ ልማት፣ የከተማ ግብርና እና የሌማት ትሩፋት፣ የሰላም ግንባታ ስራዎች፣ የገቢ አሰባሰብ፣ ልመናንና ተረጂነትን መቀነስ፣ የበጎ ፈቃድ መርሃ ግብርን በተቀናጀ የህብረተሰብ ተሳትፎ መተግበር፣ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን በአዲስ ቅኝት መምራት እና ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችን ማጠናቀቅ የእቅዱ አካል መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የተጀመሩ የኮሪደር ልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎችን በጥራት እና በተያዘላቸው የጊዜና በጀት ማጠናቀቅ እና የሚዲያና የህዝብ ግንኙነት ስራዎችን ለማጠናከር መታቀዱን ተናግረዋል። የታቀዱ ግቦችን ለማሳካት በየደረጃው የሚገኘው አመራር በቁርጠኝነትና በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት መሥራት እንደሚኖርበትም አጽንኦት ሰጥተዋል። በመድረኩ ላይ የቀረቡት የመንግሥትና የፓርቲ ዕቅዶች ከተማዋን ምቹ፣ ፅዱና ዘመናዊ የማድረግ ራዕይን መሠረት ማድረጋቸውንም ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገልጸዋል። የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብና ጥራት እንዲጠናቀቁ የሚያስችሉ በመሆናቸው ለዕቅዶቹ መሳካት መትጋት እንደሚገባ ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃንጥራር አባይ በበኩላቸው፤ በመጪዎቹ ሦስት ወራት አመራሩ በተሟላ አግባብ ለሕዝብ ቁርጠኛ አገልግሎት የሚሰጥበት ጊዜ መሆን እንዳለበት ገልጸዋል።   ከተማዋ በአሁኑ ወቅት እጅግ በርካታና ዕረፍት የሚነሱ ሥራዎች ያሉባት መሆኑን ገልጸው፤ ይህንንም አመራሩ ሊገነዘብ እንደሚገባም አሳስበዋል። በክረምቱ ወቅት የሚከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ፣ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ ከወትሮው አገልግሎት ውጭ ያሉ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እና የፕሮጀክት ክዋኔዎች ከፍተኛ ትኩረት የሚሹ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለዚህም አመራሩ ፕሮጀክቶችን ከተቀመጠላቸው ጊዜ ቀድሞ ለማጠናቀቅ የሚያስችል ከፍተኛ ተነሳሽነትን ማጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል።   በብልፅግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ ፤ በቀጣዮቹ ቀናት በአመራሩና በመዋቅሩ ውስጥ አዲስ የሥራ ተነሳሽነትና ጥንካሬ መፈጠር እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል። አሁን መዋቅሩንና አመራሩን በከፍተኛ ደረጃ በማነቃቃት እንዲሁም አባላትን በማስተባበር በ90 ቀናቶቹ የታቀዱት ሥራዎች ላይ የተጠናከረ የሥራ አፈጻጸም ማምጣት እንደሚገባና ለዚህም ዝግጁነትን አጠናክሮ መሄድ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ቡናን በበጋ መስኖ በማልማት የአምራቹን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
Jun 16, 2026 191
አዳማ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ቡናን ከመደበኛ ወቅት በተጨማሪ በበጋ መስኖ በማልማት የአምራቹን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት መደረጉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የክልሉን የቡና ምርትና ምርታማነትን በበጋ መስኖ ለማስፋፋት ያዘጋጀው የባለሙያዎችና አመራሮች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና መድረክ በአዳማ እየተካሄደ ይገኛል።   የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ መሀመድ ሳኒ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ አዲስ የቡና፣ ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ኢኒሼቲቭ ፓኬጅ ተቀርጾ ተግባራዊ እየተደረገ ነው። የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ ልማቱን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ፣ ከአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖ ጋር እያጋጠመ ያለውን የቡና ተባይና በሽታን ለመቋቋም የሚያስችል ስትራቴጂ ተነድፎ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተያዘው ስትራቴጂ ላይ ግንዛቤ እንዲፈጠር ለባለሙያዎችና ለአመራሮች ስልጠናው መዘጋጀቱን አመልክተዋል። በዚህ ረገድ በክልሉ በጥቂት ባለሀብቶች የተጀመረውንና ውጤት የተገኘበትን የበጋ መስኖ ቡና ልማት ተሞክሮ በመቀመር ወደ አርሶ አደሩ ለማስፋፋት አቅጣጫ መያዙን አስታውቀዋል። ለዚህም በየደረጃው ለሚገኙ አርሶ አደሮች የክህሎት ስልጠና በመስጠት እና የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ማዳበሪያን በማመጣጠን የቡና መስኖ ልማትን ለማስፋፋት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በዚህም አሁን ላይ በክልሉ ከአንድ ሄክታር ላይ የሚገኘውን ዘጠኝ ኩንታል ምርት ወደ 20 ኩንታል ለማሳደግ ግብ መያዙን አብራርተዋል። በቀጣይም እስከ ቀበሌ ድረስ ስልጠናዎችን በመስጠት እና የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመትከል እንዲሁም የቡና ልማትን በኩታገጠም እንዲታረስ በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ተፈጻሚ እንደሚደረግ አስረድተዋል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ተሾመ ቦጋለ በበኩላቸው፤ ቡናን በመስኖ በማልማት በሄክታር ከ30 እስከ 40 ኩንታል ምርት ማግኘት እንደሚቻል ገልጸዋል። ይህ ብቻ ሳይሆን በቂ ሙያዊ ድጋፍ ከተደረገ በዓመት ሁለት ጊዜ ምርት እንደሚሰጥም ተረጋግጧል ብለዋል።   በመሆኑም አርሶ አደሩ ያረጁ የቡና ዝርያዎችን በተሻሻሉ ዝርያዎች በመተካት እና በቂ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ማዳበሪያን በማመጣጠን ምርታማነቱን እንዲያሳድግ ኢንስቲትዩቱ ቴክኖሎጂ የማስተዋወቅ ስራ እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። እውቀት፣ ክህሎት፣ ቴክኖሎጂ እና የተፈጥሮ ጸጋን በማቀናጀት በጥቂት ዓመታት ውስጥ የቡና ምርታማነትን ከእጥፍ በላይ በማሳደግ ዘርፉ ለውጭ ምንዛሪ ግኝቱ የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከት እንደሚቻልም አረጋግጠዋል። ለአራት ቀናት በተዘጋጀው የአሰልጣኞች ስልጠና መድረክ ላይ ከክልሉ ሁሉም አካባቢዎች የተውጣጡ ከ1 ሺህ 500 የሚበልጡ የግብርና ባለሙያዎችና አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
 በቀጣዮቹ 90 ቀናት የመዲናዋን ነዋሪዎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ላይ ትኩረት ተደርጎ ይሠራል
Jun 16, 2026 158
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቀጣዮቹ 90 ቀናት የከተማዋን ነዋሪዎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ላይ በትኩረት እንደሚሠራ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ በቀጣዮቹ 90 ቀናት መሪ ዕቅድ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ አካሂዷል።   የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ ባለፉት ጊዜያት የተመዘገቡ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠልና በከተማዋ የተጀመሩ ግዙፍ የልማትና የሪፎርም ሥራዎችን በላቀ ፍጥነት ለማጠናቀቅ የ90 ቀናት መሪ ዕቅዱ ሚና የጎላ ነው ብለዋል። ዕቅዱ በዋናነት የሕዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የኮሪደር ልማት፣ የገቢ መሰብሰብ፣ የአረንጓዴ ዐሻራ፣ የኑሮ ውድነት ማቃለል፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ የክረምት በጎፈቃድ እና በመሶብ አንድ ማዕከል የሚሰጡ አገልግሎቶች ማብዛት እና ሌሎች ስትራቴጂካዊ ተግባራት ላይ ትኩረት ማድረጉን ጠቁመዋል። እንዲሁም የከተማ ግብርና፣ የሌማት ትሩፋት፣ የትምህርት ዘርፍ ማጠቃለያ እና የዝግጅት ምዕራፍ፣ የጎርፍ መከላከል ሥራ በትኩረት እንደሚከናወኑም አንስተዋል።   የታቀዱ ግቦችን ለማሳካት በየደረጃው የሚገኘው አመራር በቁርጠኝነትና በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት መሥራት እንደሚኖርበትም አጽንኦት ሰጥተዋል። በመድረኩ ላይ የቀረቡት የመንግሥትና የፓርቲ ዕቅዶች ከተማዋን ምቹ፣ ፅዱና ዘመናዊ የማድረግ ራዕይን መሠረት ማድረጋቸውንም ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገልጸዋል። የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብና ጥራት እንዲጠናቀቁ የሚያስችሉ በመሆናቸው ለዕቅዶቹ መሳካት መትጋት እንደሚገባ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን ሰብስቧል
Jun 16, 2026 153
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን መሰብሰቡን የፈንዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ደሳለኝ አምባው (ዶ/ር) አስታወቁ፡፡ የፈንዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ደሳለኝ አምባው (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የመድን ፈንዱ በተቋቋመ አጭር ዓመታት ውስጥ ለአባል የፋይናንስ ተቋማት አማራጭና ውጤታማ የፋይናንስ ሥርዓት ፈጥሯል። ከአባል ፋይናንስ ተቋማት አርቦን መሰብሰብ፣ የተሰበሰበን አርቦን በመንግስት ግምጃ ቤት ሰነድ ኢንቨስትመንትን ማሳደግና አንድ የፋይናንስ ተቋም ቢወድቅ ተቋሙን በመተካት ለገንዘብ አስቀማጮች ከ90 ቀናት ባነሰ ጊዜ መክፈል የሚያስችሉ ዋና ዋና ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በዚህም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ጨምሮ ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ ውጭ ሁሉም የግል ባንኮችና ሁሉም የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ አባል መሆናቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ እስካሁን ባለው ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን መሰብሰቡን አስታውቀዋል። ከዚህ ውስጥ 18 ነጥብ 72 ቢሊዮን ብር ከመደበኛ ተቀማጭ ገንዘብ የተሰበሰበ ሲሆን፤ ቀሪው 1 ነጥብ 89 ቢሊዮን ብር ደግሞ ከወለድ ነጻ ተቀማጭ ገንዘብ የተሰበሰበ መሆኑን አስረድተዋል። የፈንዱ አጠቃላይ የኢንቨስትመንት ክምችትም ካለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ89 ነጥብ 76 በመቶ ብልጫ በማሳየት 22 ነጥብ 98 ቢሊየን ብር መድረሱን አንስተዋል። ከጠቅላላ ኢንቨስትመንቱ 20 ነጥብ 97 ቢሊየን ብር በመንግሥት ግምጃ ቤት ሰነድ ላይ ውሏል፤ ቀሪው 2 ነጥብ 01 ቢሊየን ብር ደግሞ በሙዳራባህ የቁጠባ ኢንቨስትመንት ሂሳብ መቀመጡን አስታውቀዋል። በ2018 በጀት ዓመት 9 ነጥብ 35 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ በታቀደው መሠረት፤ እስካለፈው ዘጠኝ ወር 6 ነጥብ 76 ቢሊየን ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ የተሰበሰበውን አርቦንም በአግባቡ ኢንቨስትመንት ላይ በማዋል የፋይናንስ ተቋማትን ጤናማነትና ተወዳዳሪነት የሚያጎለብት አቅም እየተገነባ መሆኑን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ተጠሪነቱን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በማድረግ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 482/2013 መቋቋሙ ይታወሳል። የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከብሔራዊ ባንክ፣ ከኢትዮጵያ ባንኮች ማኅበርና ከኢትዮጵያ የማይክሮ ፋይናንስ ማኅበር በተውጣጡ አምስት የዳይሬክተሮች ቦርድ የሚመራ ተቋም ነው።
በክልሉ የሌማት ትሩፋት ትግበራ የወተት ምርታማነት እንዲጨምር አስተዋጽኦ አበርክቷል - ቢሮው
Jun 16, 2026 233
ሆሳዕና፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሌማት ትሩፋት የወተት ልማት ምርታማነት እንዲጨምር አስተዋጽኦ ማበርከቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የምግብ ሉአላዊነትን የማረጋገጥና ክብርን የማስጠበቅ ዓላማ ያለው ሲሆን በተለይ በወተት፣ ሥጋ፣ እንቁላልና ማር ትርፍ ምርት በማምረት መጠቀም ላይ ያተኮረ ነው። መርሀግብሩ የኢትዮጵያን ደካማ አምራችነት ታሪክ በመቀየር የምግብ ሉአላዊነትን ማረጋገጥና የኢኮኖሚ እድገትን የማፋጠን ግብም አለው። መርሃ ግብሩ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ተግባራዊ መደረግ ከጀመረ በኋላም የወተት ምርታማነትን በማሳደግ ዜጎችን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እያደረገና ገበያን ለማረጋጋት አቅም እየፈጠረ መጥቷል፡፡ በጉዳዩ ላይ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር እንደገለፁት፣ በክልሉ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የወተት ምርታማነት ለማሳደግ፣ የእንስሳት ዝርያን ለማሻሻል፣ የመኖ አቅርቦት እንዲጠናከር እንዲሁም በእንሰሳት ጤና አጠባበቅ ላይ ውጤት አምጥቷል። የወተት ምርታማነት ከማሳደግ ባለፈ የገበያ ትስስርና እሴት ጨምሮ ለገበያ ማቅረብ ላይ በመሰራቱ በክልሉ 12 የወተት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪዎች እንዲቋቋሙ መደላድል መፈጠሩንም አቶ ኡስማን ጠቅሰዋል።   በሆሳዕና ከተማ በእንስሳት እርባታ ዘርፍ የተሰማሩት አቶ አዳነ አባቴ እንደገለፁት ወደዘርፉ ከገቡ ሰባት ዓመታትን ቢያስቆጥሩም በተሻለ ተጠቃሚ ሳይሆኑ ቆይተዋል። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ትግበራን ተከትሎ መንግስት በዘርፉ የተሰማሩ ዜጎች እንዲጠቀሙ የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ሥራ መስራቱ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል። በዚህም ዝርያቸው የተሻሻሉ ጥጆችን በማግኘት የወተት ምርታማነትን እያሳደጉ ከመምጣታቸው ባለፈ ገቢያቸውም እንዲጨምር ማድረጉን ገልጸዋል።   በሀድያ ዞን ሌሞ ወረዳ ሹርሞ ዊጥቢራ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ዘነበች ጋርከቦ በበኩላቸው እንዳሉት በሌማት ትሩፋት መረሀ ግብር ታቅፈው የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው ላሞችን በማርባት በወተት ልማት ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። መንግስት በፈጠረው ዕድል ተጠቅመው ከዚህ ቀደም የነበሯቸውን የወተት ላሞች ዝርያ በተሻሻሉ ዝርያዎች በመተካት ምርታማነታቸውን እያሳደጉ መሆኑን ገልጸዋል።      
በዞኑ የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ጥያቄዎቻችንን የመለሱ ናቸው - ነዋሪዎች
Jun 16, 2026 289
አምቦ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሸዋ ዞን የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለረጅም ጊዜ ሲያነሱት የነበረውን የልማት ጥያቄ እንደመለሰላቸው የዞኑ ነዋሪዎች ገለጹ። ምዕራብ ሸዋ ዞን ከፍተኛ የግብርና ምርትና የንግድ እንቅስቃሴ ያለበት ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፣ ቀደም ሲል የነበሩት የመሰረተ ልማት እጥረቶች ምርትን በወቅቱና በጥራት ወደ ገበያ ለማቅረብ እንዲሁም ነዋሪዎች ፈጣን ማህበራዊ አገልግሎቶችን ለማግኘት ምቹ ሁኔታ እንዳይፈጠር አድርገው ቆይተዋል። ይህንን ክፍተት ለመሙላት በፌደራል፣ በክልልና በዞኑ አስተዳደር የተቀናጀ ጥረት የተገነቡት የልማት ፕሮጀክቶች በአሁኑ ወቅት ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸው በነዋሪዎች ህይወት ላይ አዎንታዊ ለውጥ በማምጣት ላይ ናቸው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የዞኑ ነዋሪዎች እንዳሉት በአሁኑ ወቅት ተጠናቀው ለአገልግሎት የበቁት የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች፣ ቀደም ሲል የነበሩትን ክፍተቶች በከፍተኛ ደረጃ በመፍታት የቆየ ጥያቄያቸውን እየመለሰላቸው ነው። ከነዋሪዎቹ መካከል የቶኬ ኩታዬ ወረዳ ነዋሪ የሆነው ወጣት ዳንኤል ባይሳ፤ በወረዳው የተከናወኑ የንጹህ መጠጥ ውሃና የመንገድ ግንባታ ስራዎች የአካባቢውን ማህበረሰብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ናቸው። በተለይም የመንገዱ መገንባት የሚያመርቱትን ምርት በቀላሉ ወደ ገበያ በማቅረብ ያጋጥም ለነበረው ችግር ዘላቂ መፍትሄ መስጠቱን ጠቁሟል። ፕሮጀክቶቹ በተለይም ለአካባቢው ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል መፍጠራቸውን ጠቅሶ፤ እሱም የዚህ እድል ተጠቃሚ መሆኑን ተናግሯል። የተገነቡ ልማቶችን ደህንነት በመጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ ከሌሎች ወጣቶች ጋር በቅንጅት እንደሚሰሩም ተናግሯል። ሌላኛዋ የአምቦ ወረዳ ነዋሪ ወይዘሮ ጋዲሴ ቡልቶ በበኩላቸው፤ ለብዙ ዓመታት በአካባቢያቸው የመንገድ መሰረተ ልማት ባለመኖሩ በኑሯቸው ላይ ከፍተኛ ችግር አድርሶባቸው እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ላይ ግን የመንገድ፣ የትምህርት ቤት እና የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው፤ የመሰረተ ልማት ዝርጋታው የቆየ ጥያቄያቸውን የመለሰና በተለይም ሴቶችን እኩል ተጠቃሚ ያደረገ በመሆኑ መደሰታቸውን ገልጸዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አበበ ጨመዳ፤ በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከ5 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ሲከናወን መቆየቱን ገልጸዋል። ከፕሮጀክቶቹ መካከል የመንገድ፣ የትምህርት፣ የጤና እና የንጹህ መጠጥ ውሃ ተቋማት ግንባታ በዋናነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ገልጸዋል። መንግስት በበጀት ዓመቱ የህዝብ ጥያቄ የነበሩ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ፣ በጥራትና በብዛት አጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት እያደረገ መሆኑንም አክለዋል። በዞኑ በ2018 በጀት ዓመት የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ 675 የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶችን ለመስራት ታቅዶ፣ እስካሁን 519 የሚሆኑት ተገንብተዋል ብለዋል። ፕሮጀክቶቹ በተቀመጠላቸው ጊዜና ጥራት እንዲጠናቀቁ የዞኑ ህብረተሰብ ያበረከተው አስተዋጽኦ የጎላ መሆኑን የገለጹት ምክትል አስተዳዳሪው፤ ለአብነትም የባህላዊ ፍርድ ቤቶች፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ እና ሌሎች የልማት ስራዎች እንዲስፋፉ ህዝቡ ትልቅ እገዛ ማድረጉን ጠቅሰዋል። በበጀት ዓመቱ የታቀዱ የልማት ፕሮጀክቶች ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቁ የዞኑን ነዋሪዎች ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ መሆኑንና ለበርካታ ስራ አጥ ወጣቶችም የስራ እድል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል። እነዚህ በህዝብና በመንግስት ተሳትፎ የተገነቡ ፕሮጀክቶች በሁለት ዙር ተከፍለው የምርቃ መርሃ ግብር እየተካሄደ መሆኑን ገልጸው፤ በመጀመሪያው ዙር 391 ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል ብለዋል። በሁለተኛው ዙር ደግሞ ግንባታቸው ሙሉ በሙሉ የተጠናቀቀ 128 ፕሮጀክቶች በቅርቡ የምርቃ መርሃ ግብር እንደሚካሄድ ገልጸዋል።    
ኮርፖሬሽኑ በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው አብሮነትን መርኅ አድርጎ ነው - ረሻድ ከማል (ዶ/ር)
Jun 16, 2026 207
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው የጋራ ተጠቃሚነትን፣ አብሮነትን እና ወንድማማችነትን መርኅ አድርጎ መሆኑን የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ኮርፖሬሽኑ የመኖሪያና የንግድ ቤቶችን ለመገንባት የሚያስችለውን ስምምነት ማድረጉን ተከትሎ፤ የደቡብ ሱዳን መንግሥት የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በጁባ ከተማ ለሚያከናውነው የዘመናዊ ቤቶች ግንባታ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን አስታውቋል።   በዚህም መሠረት፤ የሕንጻ ግንባታ ሳይቶች መረጣ እና ተያያዥ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች አፈጻጸምም በግዛቱ የኮንስትራክሽን እና ቤቶች ኮርፖሬሽን በቀረበ የጥናት ሪፖርት አማካኝነት በዝርዝር ተገምግሟል። ቀደም ሲል በአዲስ አበባ የተፈረመውን የመግባቢያ ስምምነት ወደ ተግባር የሚያስገባው ይኸው አዲስ ውልም በጁባ ከተማ መፈረሙን ኮርፖሬሽኑ ለኢዜአ የላከው መረጃ አመላክቷል። ስምምነቱን የፈረሙትም፤የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) እና የደቡብ ሱዳን ሴንትራል ኢኳቶሪያል ግዛት አሥተዳዳሪ ኢማኑኤል አድል ናቸው። በዚህም መሠረት ኮርፖሬሽኑ በጁባ ከተማ ዘመናዊ የንግድና የመኖሪያ ሕንጻዎችን የሚገነባ ይሆናል።   ከዚሁ ጋር ተያይዞ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) ከደቡብ ሱዳን መንግሥት ልዩ መልዕክተኛ አዱት ኪር ጋር ውጤታማ ውይይት አድርገዋል። ዋና ሥራ አስፈጻሚው በዚሁ ወቅት፤ የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው የጋራ ተጠቃሚነትን፣ አብሮነትን እና ወንድማማችነትን መርኅ አድርጎ መሆኑን አስገንዝበዋል። በአጭር ጊዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን አጠናቆ ግንባታውን በይፋ እንደሚጀምርም አረጋግጠዋል። አዱት ኪር በበኩላቸው፥ ኮርፖሬሽኑ በጁባ ከተማ ለሚያካሂደው የቤት ልማት ፕሮግራም የደቡብ ሱዳን የፌዴራል መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። ይህ የቤት ግንባታ መጀመር በሁለቱ እህትማማች ሀገራት መካከል ያለውን ጠንካራና ታሪካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው ያላቸውን ሙሉ እምነትም ገልጸዋል። የደቡብ ሱዳን መንግሥትም ለስምምነቱ ተግባራዊነት ያለውን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል።
የወልዲያ ከተማ የኮሪደር ልማት ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ከመሆን ባለፈ ምቹ የመዝናኛ ሥፍራ ፈጥሯል
Jun 16, 2026 175
ደሴ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በወልድያ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ከመሆን ባለፈ ምቹ የመዝናኛ ሥፍራ መፍጠሩን የከተማዋ ነዋሪዎች ገለጹ። በከተማዋ እየተከናወነ ካለው 18 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የኮሪደር ልማት ሥራ 6 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትር የሚሸፍነው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉ የሚታወቅ ነው። የኮሪደር ልማቱን በማስመልከት ኢዜአ በወልደያ ከተማ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች እንደገለጹት፣ የልማት ሥራው ለከተማዋ ተጨማሪ ድምቀት ከመሆን ባለፈ ምቹ የመዝናኛ ስፍራ ፈጥሮላቸዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ጠቅል ንጉሴ የኮሪደር ልማት ሥራው ትውልድን ታሳቢ አድርጎ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ ለልማት ሥራው ውጤታማነት የሚጠበቅባቸውን በመወጣት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። የኮሪደር ልማቱ ለወልዲያ ከተማ ተጨማሪ ውበት ከመሆን ባለፈ ለህብረተሰቡ ምቹና አማራጭ የመዝናኛ ስፍራ እየፈጠረ መምጣቱን ገልጸዋል።   ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ታሪኩ ሞገስ በበኩላቸው፣ በሌሎች ከተሞች በተከናወኑ የልማት ሥራዎች ቁጭት ቢፈጠርባቸውም በአሁኑ ወቅት በከተማዋ በተከናወኑ የልማት ሥራዎች መካሳቸውን ተናግረዋል። "የዘመናት የልማት ጥያቄያችን መልስ አግኝቷል" ያሉት ነዋሪው፣ በተለይ የኮሪደር ልማቱ የወልድያ ከተማን ውበት አጉልቶ ከማውጣት ባለፈ ከተማዋን ለኑሮና ለመዝናኛነት ምቹ ማድረጉን ገልፀዋል። በአካባቢው የሰፈነው ሰላም ለልማት ሥራ መፋጠን ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸው፣ በቀጣይም የአካባቢያቸውን ሰላም ከማጠናከር ባለፈ ለልማቱ ሲያደርጉት የነበረውን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።   በወልዲያ ከተማ የተከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ለከተማዋ ተጨማሪ ውበት ከመሆን ባለፈ ከተማዋ ለቱሪስት፣ ለኢንቨስትመንትና ለኑሮ ምቹ እንድትሆን አድርጓል ያሉት ደግሞ ሌላኛው የከተማው ነዋሪ አቶ ቸርነት እሸቴ ናቸው። በከተማዋ ቀደም ሲል የነበረው የአስፋልት መንገድ የተበላሸና ጠባብ በመሆኑ ተሽከርካሪ፣ ሰውና እንስሳት እየተጋፉ ሲጓዙ እንደነበር አስታውሰው፣ ይህም ለትራፊክ አደጋ ምክንያት ሆኖ ቆይቷል ብለዋል። የኮሪደር ልማቱ የተሽከርካሪ፣ የብስክሌት እና የእግረኛ መንገድን ከማካተቱ ባለፈ የአረንጓዴ ልማት፣ የመዝናኛ እና የልጆች መጫወቻን ጭምር አካቶ በመከናወኑ ችግሩ መፈታቱን ገልጸዋል። የወልድያ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራሬ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የከተማውን ሰላም ከማረጋገጥ ባለፈ ህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል።   በከተማው 18 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የኮሪደር ልማት ሥራ እየተከናወነ መሆኑንና ከዚህ ውስጥ 6 ነጥብ 3 ኪሎ ሜትሩ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉን አመልክተዋል። ተጠናቆ ለአገልግሎት የበቃው የኮሪደር ልማት ከስታድየም-ጎንደር በር፤ ከጎንደር በር- ሙጋድ፤ ከአዳጎ አደባባይ-ሙጋድ፤ ከአዳጎ አደባባይ -ፒያሳ እና - መነኸሪያ የተከናወኑ ልማቶችን ያካተተ እንደሆንም አስረድተዋል። ቀሪውን የኮሪደር ልማት ሥራ በአጭር ጊዜ ውስጥ አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት ህብረተሰቡን ባሳተፈ አግባብ በርብርብ እየተሰራ መሆኑንም አቶ ዱባለ ተናግረዋል።  
የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሐቆች
Jun 16, 2026 329
የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታን ጥር 2 ቀን 2018 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስጀምረውታል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ከአዲስ አበባ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት ከባሕር ጠለል በላይ በ1 ሺህ 910 ሜትር ከፍታ ላይ እየተገነባ ይገኛል። በዓመት እስከ 110 ሚሊየን መንገደኞችን የማስተናገድ ዐቅም አለው። አሁን ካለው የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የማስተናገድ ዐቅም ጋር ሲነጻጸር በ4 ነጥብ 4 እጥፍ ብልጫ ይኖረዋል።   ‎ይህ ታሪካዊ ፕሮጀክት፣ ሀገራችንን ከዓለም ቀዳሚ የአቪዬሽን ማዕከላት ተርታ ለማሰለፍ ሌሊትና ቀን በከፍተኛ ጥረት እየተገነባ ይገኛል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ በአፍሪካ ታሪክ ትልቁ የአቪዬሽን መሠረተ-ልማት ፕሮጀክት ነው። የአውሮፕላን ማረፊያው ግንባታው የሚከናወነው በሁለት ምዕራፍ ነው። የመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ 60 ሚሊየን መንገደኞች የማስተናገድ ዐቅም በመያዝ እንደ አውሮውፓውያን አቆጣጠር በ2030 እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል። በዚህ ምዕራፍ አንድ እጅግ ትልቅና ዘመናዊ እንዲሁም አንድ መለስተኛ የመንገደኞች ማስተናገጃ ተርሚናሎች ይገነባሉ። በተጨማሪም በመጀመሪያው ምዕራፍ ሁለት በተጓዳኝ የሚሠሩ የአውሮፕላን መንደርደሪያዎች እንዲሁም 180 አውሮፕላኖችን በአንድ ጊዜ ማቆም የሚያስችል ቦታ ይገነባል።   በዚሁ ምዕራፍ 350 ማረፊያ ክፍሎች ያሉት ዘመናዊ ሆቴል በተርሚናሉ ውስጥ ይገነባል። በዓመት 1 ነጥብ 5 ሚሊየን ቶን ጭነት የሚያስተናግድ የካርጎ ተርሚናል እና የአውሮፕላን ጥገና ማዕከልም በዚሁ ምዕራፍ የሚገነባ ይሆናል። ፕሮጀክቱ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ አህጉርም ትልቅ አርአያ ነው። የአፍሪካ ነፃ አኅጉራዊ ንግድ ቀጣናን ተግባራዊነት ለማቀላጠፍና የአኅጉሪቱን የንግድና የኢኮኖሚ ትስስር ለማጠናከር ቁልፍ ሚና ይጫወታል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያን ከቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጋር የሚያገናኝና በአንድ ጊዜ 12 ተሽከርካሪ ማስተናገድ የሚችል የፍጥነት መንገድ እንዲሁም ፈጣን የባቡር መንገድ ይገነባል። የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ የአፍሪካን አቪዬሽን እድገት አስሮ የያዘውን የመሠረተ-ልማት ችግር በዘላቂነት ለመፍታት የተወሰደ ትልቅ እርምጃ ነው። ይህ የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ፕሮጀክት ከፍተኛ የሥራ ዕድል ይፈጥራል። ከአውሮፕላን ማረፊያው ጋር ተያይዞ የሚመሠረተው የኤርፖርት ከተማም በንግድ፣ በኢንዱስትሪና በቱሪዝም ዘርፎች ለአካባቢው ዕድገት ትልቅ አስተዋጽዖ ይኖረዋል።
ረቂቅ አዋጁ ዘመናዊ የታክስ ሥርዓት ለመዘርጋት ትልቅ አስተዋፅኦ ያበረክታል - ቋሚ ኮሚቴው
Jun 15, 2026 491
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018(ኢዜአ)፦ የፌዴራል ታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ዘመናዊ የታክስ ሥርዓት ለመዘርጋት ትልቅ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በምክር ቤቱ የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የፌዴራል ታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የሕዝብ ይፋዊ ውይይት መድረክ አካሂዷል። በገንዘብ ሚኒስቴር የሕግ ጉዳዮች መምሪያ ኃላፊ ተወዳጅ መሀመድ የማሻሻያ አዋጁን መነሻ ሃሳብ ባቀረቡበት ወቅት እንዳሉት አዋጁ የታክስ አስተዳደሩን ቀልጣፋ በማድረግ የሀገርን ኢኮኖሚ ማሳደግ የሚያስችል ነው።   የግብር ከፋዮችን መብትና ግዴታ ሚዛናዊ በሆነ መልኩ በማስከበር ፍትሐዊነትንና ታክስ የመክፈል ግዴታን በተጠናከረ መልኩ ማስፈፀም እንደሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህም ታክስ ከፋዩ በታክስ ሥርዓቱ አመኔታ ኖሮት ግዴታውን በአግባቡ እንዲወጣ እንደሚረዳ ገልፀዋል። የገቢዎች ሚኒስትር ዴኤታ ያስሚን ወሀብረቢ የታክስ አስተዳደር አዋጁ ማሻሻያ የተቀላጠፈ ሥርዓት በመገንባት ከግብር ከፋዩ የሚነሱ ቅሬታዎችን ምላሽ መስጠት የሚያስችል እንደሆነ አስታውቀዋል። ታክስን በአግባቡ በመሰብሰብ ለሀገር ኢኮኖሚ የሚያስፈልገውን ፋይናንስ በውስጥ አቅም መሸፈን የሚያስችል ሁኔታ የሚፈጥር ነው ብለዋል።   ከሰው ንክኪ ነፃ የሆነ በዲጂታል የተደገፈ አሠራር በመዘርጋት ተደራሽነትና ቅልጥፍናን በማረጋገጥ የገቢ አሰባሰብ ሥርዓቱን ከብልሹ አሠራር ነፃ እንዲሆን ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት ጠቁመዋል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጆ በበኩላቸው ረቂቅ አዋጁ በታክስ ሥርዓቱ ላይ ተግዳሮት የሆኑ ጉዳዮችን ለማረም መዘጋጀቱን አንስተዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚሰበሰበው የታክስ ገቢ እያደገ ነው ያሉት ሰብሳቢው ይህም የማክሮ ኢኮኖሚ፣ የፊሲካል ፖሊሲና የታክስ ሥርዓት ማሻሻያዎችን ውጤታማነት የሚያሳይ መሆኑን ገልፀዋል። በግብር ከፋዩ ዘንድ እየተሠራ ያለው የግንዛቤ ፈጠራ እና ማበረታቻ የግብር ከፋዮችን ተነሳሽነት በማሳደግ ግዴታቸውን እንዲወጡ እያስቻለ እንደሚገኝም ተናግረዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር 11 ነጥብ 2 ሚሊየን ሄክታር መሬት በደን መሸፈን አስችሏል
Jun 15, 2026 583
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018(ኢዜአ)፦ ባለፉት ሰባት ዓመታት የተከናወነው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር 11 ነጥብ 2 ሚሊየን ሄክታር መሬት በደን እንዲሸፈን ማስቻሉን የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለፁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ዛሬ በቢሾፍቱ ሆራ አርሰዲ ሐይቅ ዳርቻ በይፋ አስጀምረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት በዚህ ዓመት 8 ቢሊየን ችግኞችን ለመትከል ግብ በማስቀመጥ ከፍ ወደ አደረግነው 65 ቢሊየን ችግኞች ግብ የመድረስ ትልማችንን ለማሳካት በጽናት እየገሰገስን እንገኛለን ብለዋል። የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ እንዳሉት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመረው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር መንግሥትና ሕዝብ ተቀናጅተው ያሳኩት ታላቅ ታሪክ ነው። ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ ባለፉት ሰባት ዓመታት 48 ቢሊየን ችግኞች መተከላቸውን አንስተው በየዓመቱ በአማካይ 25 ሚሊየን ዜጎች በመርሃ ግብሩ መሳተፋቸውንም ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ ከተተከሉት ችግኞች መካከል 60 በመቶ ያህሉ ለጥምር እርሻ የሚውሉ መሆናቸውን አንስተው 35 በመቶ ያህሉ ደግሞ የደን ዛፎች ናቸው ብለዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ትግበራ 11 ነጥብ 2 ሚሊየን ሄክታር መሬት በደን እንዲሸፈን ማስቻሉንም አስረድተዋል። የሀገሪቱን የደን ሽፋን ከማሳደጉ ባለፈ የአረንጓዴነት ምጣኔን በመጨመር ወደ ውሃ አካላት የሚወርደውን የደለል መጠን እንዲቀንስ አስችሏል ነው ያሉት። የአፈር መሸርሸርን በመቀነስ በየዓመቱ ወደ ወንዞች ታጥቦ ይገባ የነበረውን የአፈር ሀብት ከ2 ቢሊየን ቶን ወደ 208 ሚሊየን ቶን ዝቅ እንዲል ማስቻሉን ተናግረዋል። መርሃ ግብሩ የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርታማነትን ማሳደግ ማስቻሉን አንስተው የመድረቅ አደጋ ተጋርጦባቸው የነበሩ የውሃ አካላት እንዲያገግሙ አድርጓልም ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባትም ትልቅ አቅም እየፈጠረ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ረቂቅ አዋጁ ከፍተኛ ጥራት ያላቸው ወቅታዊ እና አስተማማኝ የስታቲስቲክስ መረጃዎች እንዲመነጩ ያስችላል
Jun 15, 2026 250
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ረቂቅ አዋጅ ከፍተኛ ጥራት ያላቸው ወቅታዊ እና አስተማማኝ መረጃዎች እንዲመነጩ፣ እንዲሰራጩና እንዲቀናጁ የሚያደርግ ብሔራዊ ስታቲስቲክስ ሥርዓት መዘርጋት የሚያስችል መሆኑን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ጥሩ ማር አባተ ገለጹ። ቋሚ ኮሚቴው የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ረቂቅ አዋጅ 23/2018 ዙሪያ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። በመድረኩም ቋሚ ኮሚቴው ግልጽነትና ማብራሪያ በሚፈልጉ ጉዳዮች ዙሪያ ከሚመለከታቸው የሥራ ኃላፊዎች ጋር ውይይት አድርጓል።   የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አዋጅ ከፍተኛ ጥራት ያላቸው ወቅታዊ እና አስተማማኝ መረጃዎች እንዲመነጩ፣ እንዲሰራጩና እንዲቀናጁ የሚያደርግ ብሄራዊ ስታቲስቲክስ ሥርዓት መዘርጋት ላይ ትኩረት ያደረገ ነው። ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት በቦርድ እንዲመራ የሚደነግግ ሲሆን የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የፖሊሲ አቅጣጫ ቁጥጥር የሚያከናውንበት እንዲሁም ዓለም የደረሰበትን ዘመናዊ አሰራርን በመከተል መረጃ ማመንጨት፣ መተንተንና ጥቅም ላይ እንዲውል ማስቻል ከዓላማዎቹ መካከል ይገኙበታል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ጥሩማር አባተ እንዳሉት፤ ረቂቅ አዋጁ በጥናት ላይ ተመስርቶ ተቋማትን ባቀናጀ አግባብ መዘጋጀቱን አብራርተዋል። የብሔራዊ የስታቲስቲክስ ሥርዓትን ለመዘርጋት እንደሚያስችል ጠቅሰው፥ ይህም የተቋማትን ሚናና ኃላፊነት በግልጽ የሚያስቀምጥ በመሆኑ የሥራ ድግግሞሽና መረጃ መፋለሶችን የሚያስቀር መሆኑን አስረድተዋል። እንደ ጂኦስፓሻል፣ ዲጂታል፣ በሴንሰር ላይ የተመሰረቱ በመስኩ ያሉ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያስችል መሆኑን አብራርተዋል። በማስረጃ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ አሰጣጥን ለማጎልበት አዋጁ ዓይነተኛ ፋይዳ እንደሚኖረውም አመልክተዋል።   የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በከር ሻሌ(ዶ/ር) እንዳሉት፤ የመረጃ አመንጪዎችን ሚስጥራዊነት መጠበቅ በረቂቅ አዋጁ በግልጽ የተቀመጠ ድንጋጌ ነው። ከመረጃ ጥራት ጋር በተያያዘም ተቋማት የሚያመነጩት መረጃ ትክክለኛና መሰረታዊ መርህን ተከትለው መረጃ እንዲያመነጩ የአቅም ግንባታ ተግባራት እንደሚከናወኑ አስረድተዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ ከዓለም አቀፍና አህጉራዊ የስታቲስቲክስ መርሆና ድንጋጌዎች ጋር በተጣጣመ መልኩ መዘጋጀቱን ጠቁመዋል።   ረቂቅ አዋጁ በስታቲስቲክስ መስክ የሚከናወኑ ተግባራትን ውጤታማ በሆነ መልኩ ለመጸፈም ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ነው ብለዋል። ይሁን እንጂ የመረጃ ሰጪዎችን ማንነትና ሚስጥራዊነት መጠበቅ ለዘርፉ ሥራ መቃናት ቁልፍ ሚና አለው ያሉት ሰብሳቢው በአዋጁ የመረጃ አመንጪዎች ግለሰቦችና ተቋማት ሚስጥራዊነት መጠበቅ ትኩረት መስጠት እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በክልሉ በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች የሚደረጉ ማበረታቻዎች አመርቂ ውጤት አምጥተዋል -ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)
Jun 15, 2026 323
አገና፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለሚሰማሩ ባለሀብቶች የሚደረጉ ማበረታቻዎች አመርቂ ውጤት ማምጣታቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በጉራጌ ዞን እዣ ወረዳ የተገነባው ቪታሳሉቲ የላሜራና ቱቦላሬ ብረት ፋብሪካን መርቀዋል። በእዚህ ወቅት ርዕሰ መስተዳድሩ እንደገለጹት በክልሉ በአምራች ኢንዱስትሪው መስክ ባለሀብቶችን በብዛት ለመሳብ በትኩረት እየተሰራ ነው።   በዘርፉ የሚሰማሩ ባለሀብቶችን ለማበረታታት በቦታ አቅርቦት፣ በመሰረተ ልማት፣ በገንዘብ ብድር እና ሙያዊ ድጋፍ እንደሚደረግ ገልጸው፤ ይህም ለዘርፉ ውጤታማነት የራሱን አስተዋጾ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ለአምራች ኢንዱስትሪዎች በሚደረጉ ማበረታቻዎች ምርትን በሚፈለገው ልክ የሚያቀርቡ ተወዳዳሪ ኢንዱስትሪዎችን ከመገንባት ባለፈ ተኪ ምርት የሚያመርቱ ኢንዱስትሪዎች እየተስፋፉ መጥተዋል ብለዋል። የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ በበኩላቸው ዛሬ የተመረቀው ፋብሪካ በዞኑ በተኪ ምርት ላይ የተሰማራ የመጀመሪያ ግዙፍ ፋብሪካ መሆኑን ተናግረዋል።   በአካባቢው በተለያዩ የኢንቨስትመት ዘርፍ ለሚሰማሩ ኢንቨስተሮች መሰረተ ልማት የተሟላላቸው ቦታዎች መዘጋጀታቸው በባለሃብቱ ተመራጭ አድርጎታል ያሉት ደግሞ የእዣ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘውዱ ዱላ ናቸው። ፋብሪካው ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ተጠቃሚ አድርጓል ብለዋል። የቪታሳሉቲ የላሜራና ቱቦላሬ ብረት ፋብሪካን ባለቤት አቶ ሰዒድ ሃጂ ኑሩ፤ ዘርፉን ለማሳደግ የተሰጠው ትኩረት እና የተመቻቸላቸውን ዕድል በመጠቀም ወደ ስራ መግባታቸውን ተናግረዋል። ለፋብሪካው ከ600 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉን ገልጸው፤ በሙሉ አቅሙ ወደስራ ሲገባ ለ123 ቋሚ እንዲሁም ለ273 ሰዎች ጊዜያዊ የሥራ ዕድል እንደሚፈጠር አስታውቀዋል።
አዲሱ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ ከአዲስ አበባ 40 ኪ.ሜ ርቀት ላይ፣ ከባሕር ጠለል በላይ በ1,910 ሜትር ከፍታ ላይ እየተገነባ ይገኛል
Jun 15, 2026 382
‎አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦አዲሱ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ፣ ከአዲስ አበባ 40 ኪ.ሜ ርቀት ላይ፣ ከባሕር ጠለል በላይ በ1,910 ሜትር ከፍታ ላይ እየተገነባ እንደሚገኝ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል፡፡ በመጨረሻው የማስተር ፕላን አቅሙ በዓመት እስከ 110 ሚሊዮን መንገደኞችን ለማስተናገድ የተወጠነ ሲሆን፣ ይህም አሁን ካለው የቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ የማስተናገድ አቅም ጋር ሲነጻጸር በ4.4 እጥፍ ብልጫ ይኖረዋልም ተብሏል።   ‎ይህ ታሪካዊ ፕሮጀክት፣ ሀገራችንን ከዓለም ቀዳሚ የአቪዬሽን ማዕከላት ተርታ ለማሰለፍ፣ በደረሰበት ሁሉ ሰንደቅ ዓላማችንን ከፍ አድርጎ የሚያሳይ እና የአኅጉራችን ኩራት በሆነው በኢትዮጵያ አየር መንገድ አማካኝነት በአፍሪካና ከዚያም ባሻገር ያለውን ትስስር ለማጠናከር ሌሊትና ቀን በከፍተኛ ጥረት እየተገነባ እንደሚገኝ ተመላክቷል፡፡
በምግብ ራስን ከመቻል እስከ የሥራ ዕድል ፈጠራ-የሌማት ትሩፋት በአዲስ አበባ
Jun 15, 2026 320
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦በሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር የተሰማሩ ዜጎች በምግብ ራሳቸውን ከመቻልና የኢኮኖሚ አቅማቸውን ከማሳደግ ባለፈ፣ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን በመዲናዋ የሚገኙ የመርሃ-ግብሩ ተጠቃሚዎች የሚናገሩት እውነታ ነው። የሌማት ትሩፋት በኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና የተመጣጠነ የምግብ አቅርቦትን በበቂ ሁኔታ ለማዳረስ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በጥቅምት 2015 ዓ.ም የተጀመረ ሀገር አቀፍ የልማት መርሃ-ግብር ነው። መርሃ-ግብሩ ዜጎች በጓሯቸው በማምረት የኢኮኖሚ አቅማቸውን እንዲያሳድጉና በምግብ ራሳቸውን እንዲችሉ በማድረግ ረገድ ትልቅ አዎንታዊ ለውጥ እያመጣ ይገኛል። ኤዜአ ያነጋገራቸው በአዲስ አበባ የመርሃ-ግብሩ ተጠቃሚዎች እንደገለጹት፤ በሌማት ትሩፋት ንቅናቄ ላይ በመሰማራት ውጤታማ መሆን ችለዋል፤ በዚህም አልፈው ለገበያ የምርት አቅርቦት መጨመር አስተዋጽኦ በማበርከት ላይ ናቸው። የመርሃ-ግብሩ ተጠቃሚ የሆነው ሰለሞን ደሳለኝ በዶሮ እርባታ ዘርፍ በመሳተፍ በቀን ከ3 ሺህ በላይ እንቁላል በማምረት በተመጣጣኝ ዋጋ ለገበያ እያቀረበ እንደሚገኝ ገልጿል።   በዚህ መርሃ-ግብር በመታገዝ ራሱንና ቤተሰቡን መደገፍ ከመቻሉ ባሻገር፣ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን አብራርቷል። በየጊዜው በመንግስት የሚደረግለት ሙያዊ ድጋፍ በዘርፉ ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን ትልቅ እገዛ እንዳደረገለትም ነው የተናገረው። በኮልፌ ክፍለ ከተማ በእንስሳት እርባታና በወተት ምርት ላይ የተሰማራው ወጣት ሰለሞን ደሳለኝ፤ በዘርፉ በመሰማራቱ ውጤታማ በመሆን ከራሱ አልፎ ቤተሰቦቹን ለመደገፍም በቅቷል።   በአሁኑ ወቅት በቀን እስከ 400 ሊትር ወተት በማምረት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሶ፣ የሚያመርቱትን የወተት ምርትም ለአካባቢው ማህበረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ እያቀረቡ መሆኑን አስታውቋል። በመርሃ-ግብሩ በአሁኑ ወቅት በርካታ ዜጎች ተሳትፈውበት በምግብ ራሳቸውን ከመቻል አልፈው፣ ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ለማህበረሰቡ ከፍተኛ ጠቀሜታ እያስገኙ መሆኑን ጨምሮ ገልጿል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ግብርና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር መሀመድ ልጋኒ፤ መርሃ-ግብሩ የኑሮ ውድነትን በመቅረፍ፣ ጤናማና አምራች ማህበረሰብ ለመገንባት፣ የሀገር ውስጥ ምርትን በማሳደግ እንዲሁም የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ረገድ ያለው አስተዋፅኦ የጎላ መሆኑንም ገልጸዋል።   በአሁኑ ወቅት የሌማት ትሩፋት መርሃ-ግብር ዜጎችን በምግብ ራሳቸውን ከማስቻል ባለፈ፣ ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ ለማህበረሰቡ ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታዎችን እያስገኘ መሆኑን አንስተዋል። በመዲናዋ በርካታ ዜጎችን በመርሃ ግብሩ በማሳተፍ በየቀኑ እስከ 3 ሚሊዮን እንቁላል እንዲሁም በየዓመቱ ከ90 ሚሊዮን ሊትር በላይ ወተት እየተመረተ ነው ብለዋል። በተለይም ቁጥራቸው ከፍተኛ ለሆኑ ወጣቶች በዶሮ እርባታ፣ በወተትና በማር ምርት ዘርፎች ሰፊ የሥራ ዕድልና አዳዲስ የገቢ ምንጮችን እየተፈጠረ መሆኑን ምክትል ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል። በተጨማሪም መርሃ-ግብሩ የተመጣጠነና ጤናማ የእንስሳት ተዋጽኦ ምግቦችን በቅርበትና በተመጣጣኝ ዋጋ በማቅረብ፣ ህብረተሰቡ ተጠቃሚ እንዲሆን እንዲሁም የዋጋ ንረትን እያረጋጋ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል።
በሐረር የተከናወነው የኮሪደር ልማት ቅርሶችን ጠብቆ ለትውልድ የሚያሻግር ተግባር ነው
Jun 15, 2026 202
ሐረር፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ)፦ በሐረር ከተማ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ቅርሶችን ጠብቆ ለትውልድ የሚያሻግር ተግባር መሆኑን በከተማዋ የሚኖሩ የተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች ገለጹ። ሐረር በተለይም ጥንታዊቷ የጀጎል ግንብ በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) የተመዘገበባት ታሪካዊና ባህላዊ የቅርስ መናኸሪያ ናት። ይህንን ህያው ታሪክና ጥንታዊ ይዘት ሳይበረዝ ለቀጣዩ ትውልድ ማሻገር ደግሞ የክልሉ ብቻ ሳይሆን የሀገር አቀፍ ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ጉዳይ ነው። በሀገሪቱ የተለያዩ ከተሞች የተጀመረውና አሁን ላይ በሐረር ከተማ እየተተገበረ ያለው የኮሪደር ልማት ሥራ ዋና ዓላማም የከተማዋን መሰረተ ልማት ማዘመን፣ የነዋሪዎችን የኑሮ ደረጃ ማሻሻልና ከተማዋን ለቱሪስት መስህብ ይበልጥ ምቹ ማድረግ ነው።   አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የከተማዋ ነዋሪዎች፤ በከተማዋ የተከናወነው የኮሪደር ልማት ሥራ የከተማዋን ታሪካዊ ቅርሶች በጠበቀና በተንከባከበ መልኩ የተሰራ በመሆኑ፣ ለቀጣዩ ትውልድ የሚተርፍ ትልቅ አሻራ ማሳረፉን ገልጸዋል። "ውልደቴና እድገቴ ጀጎል ነው" ያሉን 80 ዓመት እድሜ ባለፀጋ አቶ መሀመድ ዩስፍ ቀደም ሲል ጀጎልን ጨምሮ ሌሎች በውስጡ የሚገኙ ቅርሶች በቆሻሻና በተለያዩ ምክንያት የመፍረስ አደጋ ተጋርጦባቸው እንደነበር አስታውሰዋል። ኮሪደር ልማቱ ቀደም ሲል የታዩ ችግሮችን የታደገ፣ ለአዛውንቶችና ህጻናት ማረፊያና መዝናኛ የፈጠረ፣ የሐረርን ቀደምት ስልጣኔና ታሪክ በሚመጥን መልኩ የተገነባ መሆኑን ተናግረዋል።   "ሐረር አሁን ነው የደመቀችው፤ በከተማው በገጠሩና በጀጎል የተሟላ የኮሪደር ልማት ስራ ተከናውኗል" ያሉት ደግሞ አባገዳ አህመድ ዩስፍ ናቸው። የኮሪደር ልማቱ ልጆች በአግባቡ እንዲጫወቱ ምቾት ከመፍጠር ባለፈ መንፈስን የሚያድስ አብሮነትና አንድነትን ያጠናከረ ገጸ በረከት ስለማበርከቱ አንስተዋል። ወይዘሮ እጸገነት ውቤ በበኩላቸው፤ ለልጅ ልጆቻችን የሚተርፍ የኮሪደር ልማት ስራ ተከናውኗል ብለዋል። መንግስት በከተማም ሆነ በገጠር ያከናወናቸውን ስራዎች ሐረር የቱሪስት መዳረሻዎቿ እንዲጎለብቱ ከማስቻሉ ባለፈ ለሴቶችና ወጣቶች የስራ ዕድል በመፍጠር ተጠቃሚ አድርጓል ብለዋል። የኮሪደር ልማቱ ስራ እየጠፋች የነበረችውን ሐረርን የመለሰና ለስራና ለመዝናኛ ምቹ የሆነችውን ሐረርን ያሳየን ነው ያሉት ደግሞ ወይዘሮ መሊካ ዘከሪያ ናቸው። የኮሪደር ልማት ስራው የብስክሌት፣ የተሽከርካሪና የእግረኛ መንገድን ያካተተ በመሆኑ ለእግረኛና ለተሽከርካሪ ምቹ ሁኔታን የፈጠረ ነው ብለዋል። የከተማውን ውበት ከማጉላት ባለፈ የህብረተሰብ ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚረዱ መሰረተ ልማቶችም የተዘረጉባት መሆኑን አንስተዋል።   በክልሉ የኮሪደር ልማት ስራ ባህልና ቅርስን በጠበቀ መልኩ ስለመከናወኑ የተናገሩት ደግሞ የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ምክትል ሃላፊ ረዒስ ዩስፍ ናቸው። ተቋማትንና ህብረተሰቡን በማስተባበር በጀጎል ውስጥ እና ዙሪያው እንዲሁም በከተማው የኮሪደር ልማት ስራው መከናወኑን አንስተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም