ኢኮኖሚ - ኢዜአ አማርኛ
ኢኮኖሚ
ኩታ ገጠም እርሻን በማስፋፋት ምርታማነትን ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የባለድርሻ አካላት ሚና ወሳኝ ነው
Jun 11, 2026 408
ወላይታ ሶዶ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ኩታ ገጠም እርሻን በማስፋፋት ምርታማነትን ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የባለድርሻ አካላት ሚና ወሳኝ መሆኑን በግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የደቡብ ማዕከል አስታወቀ። ማዕከሉ በሲዳማ፣ በደቡብ ኢትዮጵያ እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች በግብርና ልማት ሥራ የተሰማሩ ኩባንያዎች ተግባራት አፈጻጸምን የሚገመግም መድረክ በወላይታ ሶዶ ከተማ አካሂዷል። በኢንስቲትዩቱ የደቡብ ማዕከል የግብርና ኮሜርሻላይዜሽን ክላስተር ዳይሬክተር አቶ ተሰማ ህርባዬ እንዳሉት፤ አርሶ አደሮችን በኩታ ገጠም ግብርና ቢዝነስ ኩባንያዎች በማደራጀት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እየተሰራ ነው። ለዚህም ማዕከሉ በተመረጡ ወረዳዎች በኩታ ገጠም እርሻ አርሶ አደሮችን በማደራጀት ምርታማነታቸው እንዲያድግና የገበያ ትስስር እንዲያገኙ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ኩታ ገጠም እርሻ አርሶ አደሩ የግብአት አቅርቦትን በቀላሉ የሚያገኝበት አውድ ከመፍጠሩ ባለፈ የሜካናይዝድ እርሻን በመተግበር ምርትና ምርታማነቱን ለማሳደግ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል። ኩታ ገጠም እርሻን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የባለድርሻ አካላት ሚና ወሳኝ መሆኑንም አስገንዝበዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትልና የእርሻ ዘርፍ ኃላፊ አቶ አድማሱ አወቀ በበኩላቸው እንዳሉት፤ በክልሉ ግብርናን በማዘመን የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ ግብ ተጥሎ እየተሰራ ነው። ለዚህም ቢሮው ከግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር የተለያዩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን ለአርሶ አደሮች እያደረሰ ይገኛል ብለዋል። ይህም አርሶ አደሩ የግብርና ምርቶቹን በጥራትና በብዛት ለገበያ በማቅረብ ተወዳዳሪ እንደሚያደርገው ነው የተናገሩት። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጉራጌ ዞን የቸሃ ወረዳ ግብርና ቢዝነስ ኩባንያ አባል አርሶ አደር አብዱራሃማን ሙክታር፤ ከዚህ ቀደም በተናጠል ባከናወኑት የእርሻ ስራ ብዙም ሳይጠቀሙ ቆይተዋል። በአሁኑ ወቅት በኩታ ገጠም እርሻ ተደራጅተው ኩባንያ ከፈጠሩ ወዲህ ጉልበታቸውን በማስተባበር እንዲሁም ግብአትና ቴክኖሎጂ በመጠቀም ምርታማነታቸውን እንዳሳደጉ ተናግረዋል። ይህም ምርታቸውን ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ የተሻለ ገቢ በማግኘት የቤተሰባቸውን ኑሮ ለማሻሻል እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። በስልጤ ዞን የሳንኩራ ወረዳ ግብርና ቢዝነስ ኩባንያ አባል ወይዘሮ አሚና ሃጂ ጀማል በበኩላቸው፤ 85 ወንዶች እና 15 ሴቶች በግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ተደራጅተው የጓሮ አትክልትና ሌሎች ምርቶች እያመረቱ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዚህም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ተጠቃሚ እየሆኑ ከመምጣታቸው ባለፈ ገበያን በማረጋጋት የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ተናግረዋል። በመድረኩ ከደቡብ ኢትዮጵያ፣ ከማዕከላዊ እና ከሲዳማ ክልሎች የተውጣጡ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በክልሉ የግብርና ግብዓትና የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሻሻል ምርታማነትን ለማሳደግ የተጀመረው ሥራ ይጠናከራል
Jun 11, 2026 276
ሃዋሳ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል የግብርና ግብዓት እና የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሻሻል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። በክልሉ በዘንድሮው የመኸር ወቅት ከ169 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዶ ዝግጅት መደረጉን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታውቋል፡፡ የሲዳማ ክልል የዘንድሮ መኸር እርሻ የንቅናቄ መድረክ ዛሬ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ እንደተናገሩት በክልሉ በግብርና ልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ገበያን ለማረጋጋት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በተያዘው የመኸር ወቅትም የግብርና ግብዓትና ቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በማሻሻል ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ በትኩረት እንደሚሰራም አስገንዝበዋል። በዚህም የቤተሰብ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ገበያን ለማረጋጋት የሚያስችል ትርፍ ምርት እንዲመረት አመራሩ ድጋፍና ክትትሉን ማጠናከር አለበት ሲሉም አክለዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው እንዳሉት በክልሉ በዘንድሮ የመኸር ወቅት ከ169 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ በማልማት ከ16 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዷል። በምርት ዘመኑ የማሳ ሽፋንን ለማሳደግ እና ምርታማነትን ለሚጨምሩ ግብዓትና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ትኩረት እንደሚሰጥ የጋራ መግባባት ላይ መደረሱንም ተናግረዋል። ለግብርና ሥራው ከማሳ ዝግጅት ጀምሮ የምርጥ ዘርና የማዳበሪያ አቅርቦት በበቂ ሁኔታ መኖሩን አቶ መምሩ ገልጸው፣ በዓመቱ በክልሉ ከ300 ሺህ ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለማቅረብ ታቅዶ እስካሁን ድረስ ከ75 ከመቶ በላይ የሚሆነውን ለማሳካት ተችሏል ብለዋል። በመኸር እርሻው የግብርና ግብዓትና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ላይ ለውጥ በማምጣት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት እንደሚሰራም አመልክተዋል። የዛሬው መድረክ በምርት ዘመኑ ለተያዘው ዕቅድ ስኬታማነት አመራሩ የጋራ መግባባት ላይ እንዲደርስ ማድረጉን የተናገሩት ደግሞ የሰሜናዊ ሲዳማ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርናና ገጠር ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ ዱሬሳ ሌዳሞ ናቸው፡፡ በዞኑ በዘንድሮ የመኸር ወቅት ከ43 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በማልማት ከ4 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱንም ተናግረዋል። ለዚህም የቴክኖሎጂና የግብዓት አጠቃቀም ላይ ለውጥ በማምጣት ምርትና ምርታማነትን የማሳደግ ሥራ ይሰራል ብለዋል፡፡ በንቅናቄ መድረኩ ላይ በየደረጃው ያሉ ባለድርሻ አካላት የተሳተፉ ሲሆን ለዘንድሮ የመኸር እርሻ ልማት የተዘጋጁ ሰነዶችም ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል።
የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በሁሉም የኢኮኖሚ አመላካቾች የተመዘገቡ ስኬቶችን ለማስቀጠል ታሳቢ ያደረገ ነው
Jun 11, 2026 493
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በሁሉም የኢኮኖሚ አመላካቾች የተመዘገቡ ስኬቶችን ለማስቀጠል ታሳቢ ያደረገ መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገለጹ፡፡ በ6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመኑ 25ኛ መደበኛ ስብሰባ የ2019 በጀት ዓመት የፌዴራል መንግሥት የበጀት መግለጫ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል፡፡ ምክር ቤቱም በቀረበው የ2019 የበጀት መግለጫ ላይ ከተወያየ በኋላ ለፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለዝርዝር ዕይታ መርቶታል፡፡ የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ለምክር ቤት ባቀረቡት የ2019 በጀት ዓመት የበጀት መግለጫ እንደገለጹት፤ የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያውና የአስር ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ ትግበራ ስኬታማ ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ውስጣዊና ውጫዊ ጫናዎችን በብቃት በመቋቋም ጠንካራ አፈጻጸም ማስመዝገቡን ገልጸው፤ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው አበርክቶ የጎላ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከ2012 እስከ 2016 ባሉት የበጀት ዓመታት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በአማካይ በየዓመቱ የ6 ነጥብ 8 በመቶ ዕድገት ያስመዘገበ እንደነበር በማስታወስ፤ በ2017 በጀት ዓመት የ9 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት ተመዝግቧል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ በዘንድሮው በጀት ዓመት የመካከለኛው ምሥራቅ የተፈጠረውን ዓለም አቀፍ ጫና ጭምር በመቋቋም የ10 ነጥብ 2 በመቶ ዕድገት ታስመዘግባለች ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ በዓለም ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እያስመዘገቡ ካሉ ሀገራት ተርታ የሚያሰልፋትን ስኬት ማስመዝገቧን ገልጸው፤ ይህም የተቀናጀ የገንዘብና ፊሲካል ፖሊሲው ውጤት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ይሄውም የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በጠንካራ መሠረት ላይ የተገነባ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ የሸቀጦችን የዋጋ ግሽበት ወደ ነጠላ አሃዝ ማውረድ አስችሏል ብለዋል፡፡ በተያዘው በጀት ዓመት የኢኮኖሚ አፈጻጸሙ በጥሩ አፈጻጸም ላይ እንደሚገኝ በማንሳት፤ ስኬቱ የተረጋጋና የበለጸገ ኢኮኖሚ ለመገንባት የተጀመረውን ጥረት እንደሚያጠናክር ገልጸዋል፡፡ የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀትም በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በሁሉም የኢኮኖሚ አመላካቾች የተመዘገቡ ስኬቶችን ለማስቀጠል ታሳቢ ተደርጎ የተዘጋጀ ነው ብለዋል፡፡ በ2019 በጀት ዓመት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ 10 ነጥብ 1 በመቶ እድገት እንደሚያስመዘግብ እንደሚጠበቅና የቀረበው ረቂቅ በጀትም የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውን በተሳካ ሁኔታ ገቢራዊ ለማድረግና የመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት የሚፈጥረውን የኢኮኖሚ ጫና ጨምሮ የውጭ ኢኮኖሚያዊ ቀውሶችን ለመቋቋም ያለመ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በበጀት ዓመቱ የፌደራል መንግስትን ጠቅላላ ገቢ 1 ነጥብ 817 ትሪሊየን ብር ለማድረስ ታሳቢ መደረጉን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ ከዚህ ውስጥ 1 ነጥብ 6 ትሪሊየን ብር የሚሆነው ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ገቢዎች ለመሰብሰብ መታቀዱን አመላክተዋል። ለ2019 በጀት ዓመት የቀረበው አጠቃላይ 2 ነጥብ 339 ትሪሊየን ብር በጀት ከዘንድሮው በጀት ዓመት አንጻር የ21 ነጥብ 3 በመቶ እድገት እንዳለው ገልጸዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በተለያዩ ዘርፎች ተጨባጭ ውጤቶችን ማስመዝገቧን ገልጸዋል፡፡ ሪፎርሙ የውጭ ምንዛሪ በገበያ እንዲወሰን በማድረግ የውጭ ምንዛሪ ክምችትን ማሳደግ፣ የዋጋ ግሽበትን ወደ ነጠላ አሃዝ መውረድና የውጭ ኢንቨስትመንት ፍሰትን ማሳደግ አስችሏል ብለዋል፡፡ ለ2019 በጀት ዓመት የቀረበው ረቂቅ በጀት ከባለፈው ዓመት የላቀ መሆኑ የመንግሥትን ግዙፍ የልማት ዕቅዶች ለማሳካት ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡
በክልሉ በህብረተሰቡ ተሳትፎ ከተሞች ገጽታቸው እየተቀየረ ነው
Jun 11, 2026 209
ዲላ ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከተሞችን በህብረተሰብ ተሳትፎ ገጽታቸውን በመቀየር ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ ማድረግ መቻሉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ ገለጹ። በጌዴኦ ዞን ይርጋጨፌ ከተማ 100 ሚሊዮን ብር በሚጠጋ ወጪ በህብረተሰብ ተሳትፎ የተገነቡ የመሠረተ ልማቶች ዛሬ ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል። ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በወቅቱ እንዳሉት፤ በክልሉ ህብረተሰቡ ከመንግስት ጋር በመቀናጀት በሚያከናውናቸው ተግባራት የከተሞች የተጎሳቆለ ገጽታ እየተቀየረ ነው ብለዋል። ዛሬ በይርጋጨፌ ከተማ ለአገልግሎት የበቁ መሠረተ ልማቶች የዚሁ ማሳያ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በከተማው በኮሪደርና በወንዝ ዳርቻ ልማት የተጀመሩ መሠረተ ልማቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉና የውስጥ አቅምን አስተባብሮ ብልጽግናን የማረጋገጥ ሥራ መጠናከር እንዳለበት አሳስበዋል። በከተማው ሰው ተኮር የሆኑ ልማት ስራዎች ትኩረት የተሰጣቸው መሆኑን ጠቁመው በመኖሪያ ቤት አቅርቦት በኩል እየተከናወነ ያለው ስራም ተጠቃሽ መሆኑን አመልክተዋል ። በዞኑ ከተሞችን ውብና ጽዱ እንዲሁም ለኑሮና ለኢንቨስትመንት ምቹ ከማድረግ አንጻር ውጤታማ ተግባር መከናወኑን ያነሱት የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ናቸው። በዞኑ በሚገኙ ከተሞች የዜጎችን የቤት ፍላጎት ለማሟላት የጋራ መኖሪያ ቤቶች እየተገነቡ ይገኛል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው ከተሞችን ፅዱና ለነዋሪዎች ምቹ የማድረግ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል። የይርጋጨፌ ከተማ ከንቲባ አቶ ብዙአየሁ ታደሰ በበኩላቸው ፤ በህብረተሰብ ተሳትፎ ለአገልግሎት የበቁት የመሠረተ ልማት ተቋማት ለህብረተሰቡ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡ ናቸው ብለዋል። ዛሬ ለአገልግሎት የበቁ መሰረተልማቶች የሌማት ትሩፋት ምርቶች መሸጫ ሼዶች፣ ድልድይ፣ መማርያ ክፍሎች እንዲሁም 40 መኖርያ ቤቶችን ያካተተ መሆኑን ጠቁመው ለመሰረተ ልማቶቹ ግንባታ 100 ሚሊዮን ብር ወጪ መደረጉን አንስተዋል። በከተማዋ መሶብ አንድ ማዕከልና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራ እየተፋጠነ እንደሚገኝና በቀጣይ ወር ለአገልግሎት እንደሚበቁ ተናግረዋል።
በክልሉ የዘር ጥራትና መጠንን በማላቅ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Jun 11, 2026 163
ወላይታ ሶዶ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ ዘር በዓይነት፣ በመጠንና በወቅቱ በማቅረብ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው በግብርና ግብዓትና ገጠር ፋይናንስ አቅርቦት ዘርፍ እና በክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የዘር ብዜት ዕቅድ አፈጻጸምና ዝግጅት ላይ ያተኮረ የባለ ድርሻ አካላት የውይይት መድረክ በወላይታ ሶዶ ከተማ እያካሄደ ይገኛል። በመድረኩ የተገኙት የቢሮው ምክትል ኃላፊና የግብርና ግብዓትና ገጠር ፋይናንስ አቅርቦት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ግዳልቅ አልቅሚ እንደገለጹት፤ በክልሉ የዘር ጥራትና መጠንን በማላቅ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል። ይህም የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ፣ ለኢንዱስትሪዎች በቂ ግብዓትን ለማቅረብና የሥራ ዕድሎችን ለመፍጠር የሚያግዝ ነው ብለዋል። ለዚህ ስኬት ደግሞ የዘር አቅርቦትን በዓይነት፣ በመጠንና በወቅቱ ማሟላት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህም በ2017/18 የምርት ዘመን በክልሉ ከ2 ሺህ 200 ሄክታር በላይ መሬት ላይ ከ30 ሺህ ኩንታል በላይ ምርጥ ዘር ማምረት መቻሉንም ገልጸዋል። የአርሶ አደሮችን የዘር ፍላጎት በማሟላት ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር የባለድርሻ አካላት ትብብር ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል። ለዚህም ማነቆዎችን በጋራ በመፍታት የዘር ብዜት አስተዳደርን ማጠናከር እንደሚገባ ነው የተናገሩት። የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ምክትል ዳይሬክተር ያሲን ጎአ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በክልሉ የሚገኙ የምርምር ማዕከላትን ፍላጎት መሰረት ባደረገ መልኩ ዘር በማባዛት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በልዩ ትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የአርሶ አደሮች ምርትና ምርታማነት እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። የምርጥ ዘር ብዜቱ ዓላማ የጥራጥሬ፣ የስራ ስር ሰብሎችንና የፍራፍሬዎች እንዲሁም የዓሳና የእንስሳት ዝርያዎችን በውጤታማነት በመከወን የክልሉን ፍላጎት ተደራሽ ማድረግ መሆኑን አመልክተዋል። ይህን ለማስቀጠል ደግሞ ከክልሉ ግብርና ቢሮ እንዲሁም ከዘርፉ ባለድርሻ አካላት ጋር የተጀመረው ቅንጅት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
በፓርኩ የአዳዲስ ኩባንያዎች ተሳትፎ ማደጉ የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት እየጨመረው ነው
Jun 11, 2026 208
ሀዋሳ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ የአዳዲስ ኩባንያዎችን ተሳትፎ በማሳደግ የዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት እንዲጨምር መደረጉን የሲዳማ ክልል ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን አስታወቀ። የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሀይሉ የተራ እንደገለጹት፤ በፓርኩ የሀይል አቅርቦትና የፍሳሽ ማጣሪያን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ መሰረተ ልማቶች መሟላታቸው ባለሀብቱን እየሳበ ነው። በዚህም በፓርኩ የዜጎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚነትና የውጭ ምንዛሬ ግኝት የሚያጠናክሩ አዳዲስ ኩባንያዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ገልጸው፣ ቡናና ሙዝ ማቀነባበርን ጨምሮ በአዳዲስ የሥራ ዘርፎች የተሰማሩ ኩባንያዎች ወደስራ መግባታቸውን ተናግረዋል። በተለይም የሙዝ ምርትን ወደችብስነት መቀየርና ቡናን በቀጥታ አቀነባብሮ ወደውጭ ገበያ የሚያቀርቡ ኩባንያዎች አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማስተዋወቅ፣በሥራ ዕድል ፈጠራና በገበያ ትስስር ልዩ ዕድል ይዘው የመጡ ናቸው ብለዋል። በፓርኩ አዲስ ወደስራ ከገቡ ኩባንያዎች መካከል የ"ኤፔክስ ማኑፋክቸርንግና ትሬዲንግ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ድርጅት" መስራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ መስፍን ተፈራ፣ ድርጅቱ የሙዝ ምርትን በማቀነባበር ችፕስ እያመረተ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከ200 በላይ ዜጎች በድርጅቱ ቋሚ የሥራ ዕድል እንደተፈጠረላቸው ገልጸው፣ በሲዳማና አጎራባች አካባቢዎች ለሚገኙ የሙዝ አምራች አርሶ አደሮችም የገበያ ትስስር ተፈጥሯል ብለዋል። አቶ መስፍን እንዳሉት ድርጅቱ ከ700 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ዘንድሮ ወደስራ የገባ ሲሆን በቀን እስከ 20 ሺህ ኪሎ ግራም ሙዝ በመፍጨት ወደችፕስነት በመቀየር ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ያቀርባል። በፓርኩ በዘንድሮ ዓመት ከ2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ብር በላይ በሆነ በጀት ወደስራ የገባው የቻይናው የመይመይ የቡና ፕሮሰሲንግ ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ድርጅት ተወካይ ሚስተር ጄይ ሴን በበኩላቸው፤ በፓርኩ ውስጥ ለሥራ ምቹ ሁኔታ መኖሩን ገልጸዋል። ድርጅቱ ቡናን ከአርሶ አደሩ ማሳ በቀጥታ ተቀብሎና አቀነባብሮ በቀጥታ ለዓለም አቀፍ ገበያ እንደሚያቀርብ ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅትም ወደተግባር እየገባ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በቡና ልማት የተሰማሩ በርካታ አርሶ አደሮችን ካቀፉ 10 ማህበራት ጋር የገበያ ትስስር መፍጠሩን የገለጹት ሚስተር ጄይ፣ ድርጅቱ በሙሉ አቅሙ ሲንቀሳቀስ ከ750 ለሚበልጡ ዜጎች ቋሚ የሥራ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል፡፡ በኩባንያዎች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል ዶክተር ታምር ጌታቸው እና ወይዘሮ ራሔል አስናቀ በፋብሪካዎች በመቀጠር የስራ ዕድል ተጠቃሚ በመሆን በሚያገኙት ገቢ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን እያስተዳደሩ መሆናቸውን ጠቅሰዋል ። በ2012 ዓም ወደሥራ የገባው ይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ ፓርክ በ294 ሄክታር መሬት ያረፈ ሲሆን አስፈላጊ መሰረተ ልማቶችም የተዘረጉለት ነው። ፓርኩ አዳዲስ ኩባንያዎችን በመሳብ እና ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር ረገድ አበረታች ውጤት እያስገኘ ሲሆን ለክልሉ ኢኮኖሚያዊ እድገትም ትልቅ አቅም ይፈጥራል።
የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ ስኬታማ ውጤቶች ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ማዕከል አድርጓታል
Jun 11, 2026 428
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ ስኬታማ ውጤቶች ሀገሪቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ማዕከል ተደርጋ እንድትታይ ማድረጉን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ ገለጹ። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመኑ 25ኛ መደበኛ ስብሰባውን አካሂዷል። በስብሰባውም የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ የፌዴራል መንግሥት የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀትን በተመለከተ በሚያቀርቡት የበጀት መግለጫ ላይ ይወያያል። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ፤ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የቀረበውን የፌዴራል መንግሥት የ2019 ዓ.ም በጀት ዓመት ረቂቅ በጀትን አስመልክቶ መግለጫ አቅርበዋል። በመግለጫቸው፤ ከ2017 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ በተደረገው የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የውጭ ክፍያ ሚዛን ጫናና የውጭ ምንዛሬ እጥረት ተግዳሮቶችን በእጅጉ መቅረፍ ተችሏል ብለዋል። የገበያ መር የውጭ ምንዛሬ አስተዳደር ሽግግሩም የውጭ ምንዛሬ እጥረትን ከመቅረፉ ባለፈ፣ በሕጋዊና በትይዩ (ጥቁር) ገበያ መካከል የነበረውን የተመን ክፍተት በከፍተኛ ደረጃ አጥብቦታል ብለዋል። በዚህም በ2017 በጀት ዓመት የሸቀጦች ወጪ ንግድ ገቢ በ2016 ከነበረበት 3 ነጥብ 8 ቢሊዮን ዶላር ወደ 8 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር ዕድገት በማስመዝገብ የ119 በመቶ ከፍተኛ ጭማሪ ማሳየቱን ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በመገባደድ ላይ በሚገኘው በዚህ በጀት ዓመትም የወጪ ንግድ ከፍተኛ አፈጻጸም በመቀጠሉ የንግድ ሚዛን ጉድለቱ በከፍተኛ ደረጃ ቀንሷል ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን የኢትዮጵያ ታላቁ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ተጠናቆ ኃይል ማመንጨቱ ምርታማነትን ከመጨመር ባለፈ፣ ጎረቤት ሀገራትን የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ በማድረግ ተጨማሪ የውጭ ምንዛሬ ምንጭ እየፈጠረ መሆኑን ጠቅሰዋል። የገንዘብ ፖሊሲ ማሻሻያውን በተመለከተም፤ ማሻሻያው የፋይናንስ ዘርፉን ውጤታማና ጤናማነት በማረጋገጥ የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያሳልጥ ዘመናዊና ገበያ መር የወለድ ምጣኔ እንዲፈጠር ማድረጉን አስረድተዋል። ይህም የንግድ ባንኮች ከደንበኞቻቸው ጋር በገበያ ሁኔታዎች ላይ በመመስረት የወለድ ተመኖችን እንዲደራደሩና እንዲወስኑ ሙሉ መብት አስገኝቶላቸዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክም የተዘረጋውን ዘመናዊ የገንዘብ ፖሊሲ የሚያጠናክሩ በርካታ ለውጦችን በመተግበር የፋይናንስ ዘርፉን ደህንነት ለማስጠበቅና ለማዘመን እየሠራ ይገኛል። እንዲሁም የኢትዮጵያ ሰነደ መዋለ ንዋይ (ካፒታል) ገበያ መመስረቱ ዘመናዊ የካፒታል ሥርዓትን በመዘርጋት፣መንግሥትና ኩባንያዎች የረጅም ጊዜ የፋይናንስ ፍላጎታቸውን ማሰባሰብ የሚችሉበትን ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል። የተሟላ ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ዝቅተኛ ገቢ ባለው የሕብረተሰብ ክፍል ላይ የሚያስከትለውን የኑሮ ጫና ለመቋቋም መንግሥት ኃላፊነት በተሞላበት መንገድ የማኅበራዊ ድጎማ ወጪዎችን ተግባራዊ ማድረጉን ሚኒስትሩ አብራርተዋል። በዚህም መሠረት በነዳጅ፣ በአፈር ማዳበሪያ፣ በልማታዊ ሴፍቲኔት፣ በምግብ ዘይት፣ በመሠረታዊ መድኃኒቶች እንዲሁም በፌዴራልና በክልል የመንግሥት ሠራተኞች የደመወዝ ጭማሪ ላይ ከፍተኛ የበጀት ድጎማ ተደርጓል። ባለፉት ዓመታት የተመዘገቡት የኢኮኖሚ ዕድገት ውጤቶች የውጭ ባለሀብቶችን ቀልብ በመሳብ ኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት መዳረሻቸው እያደረጓት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በአጠቃላይ በተያዘው በጀት ዓመት የ10 ነጥብ 2 በመቶ ጥቅል ሀገራዊ ዕድገት (GDP) ማስመዝገብ እንደሚቻል በርካታ የኢኮኖሚ አመላካቾች ያሳያሉ ብለዋል።
በአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራን ከኢኮኖሚ ፍላጎት ጋር የሚያጣጥም ክህሎትና ብቃት ልማት ላይ ኢንቨስት ማድረግ ይገባል
Jun 11, 2026 389
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራን ከኢኮኖሚ ፍላጎት ጋር የሚያጣጥም የዜጎች ክህሎትና ብቃት ልማት ላይ ኢንቨስት ማድረግ እንደሚገባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሀፊ ክሌቨር ጋቴቴ ገለጹ። በሥራ ፈጠራ ላይ ትኩረቱን ያደረገ የአፍሪካ ዴቨሎፕመንት ኢምፓክት ፎረም 2026 በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) መካሄድ ጀምሯል። የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሀፊ ክሌቨር ጋቴቴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የአፍሪካን መጻኢ ዕድል ለመወሰን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጥ ኢንዱስትሪ ምኅዳር መገንባት ይገባል ብለዋል። ከዓለም አቀፍ አኳያም አህጉሪቷ የታደለችውን ስትራቴጂክ የሰው ሃብት የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማረጋገጥ አህጉራዊ ዕድገትና ብልፅግናን ማረጋገጥ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ለዚህም የአፍሪካ ሀገራት መንግሥታት፣ ዩኒቨርሲቲዎች፣ የምርምር ተቋማት፣ የሥራ ፈጣሪዎች፣ የልማት ተቋማትና የግል ማኅበራት አዳዲስ መፍትሄዎችን እያፈለቁ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ፎረሙም የአፍሪካዊያንን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት ለማሻሻል ተግባራዊ መፍትሄዎችን ለማራመድ ፖሊሲ አውጪዎችን፣ ባለሀብቶችንና የልማት አጋሮችን የሚያገናኝ መሆኑን ጠቅሰዋል። የአህጉሪቷ ዜጎችን በሚፈለገው መጠን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ሁሉንም ያካተተ ምቹ ሥነ-ምህዳር መገንባት እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። ለዚህም ከአፍሪካ የኢኮኖሚ ዕድገት ፋላጎቶች ጋር የሚጣጣሙ የዜጎች ክህሎትና ብቃት የሚያጎለብት ኢንቨስትመንትን ማሳደግ እንዲገባ አስገንዝበዋል። ለወጣቶችም የትምህርት ሥርዓቶችን የሚያጠናክር የዲጂታል ስልጠና በማሳደግ በነባርም ሆነ አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ክህሎቶች ማስታጠቅ እንደሚገባ ተናግረዋል። ለዚህም አዳዲስ ጀማሪ ስራዎችን (start-ups) መደገፍ እንደሚገባ ጠቁመዋል። የአፍሪካን ኢንዱስትሪ ልማት ከእሴት ሰንሰለት ጋር በማሰናሰል የአህጉሪቷ ዕድገትና ብልጽግናን ማፋጠን እንደሚያስፈል ጠቁመዋል። አፍሪካ ጥሬ ዕቃዎችን ወደ ውጭ በመላክ እና የተጠናቀቁ ምርቶችን ወደ ውስጥ በማስገባት በቂ የሥራ ዕድል መፍጠር እንደማትችል አጽንኦት ሰጥተዋል።
በጅማ ዞን በዚህ ዓመት ከ 12 ሺህ በላይ ነዋሪዎች የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ ሆነዋል
Jun 11, 2026 87
ጅማ፤ ሰኔ 4/2018(ኢዜአ)፡- በጅማ ዞን በበጀት ዓመቱ ከ 12 ሺህ በላይ ነዋሪዎች የኤሌክትሪክ ተጠቃሚ መሆናቸውን የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ጅማ ሪጅን ገለጸ። የሪጅኑ ዳይሬክተር አቶ ሲሳይ ሰቦቃ፣ በበጀት ዓመቱ የዞኑ ነዋሪዎችን የመብራት ተደራሽነትን ለማስፋፋት በትኩረት ሲሠራ መቆየቱን ገልጸዋል። በዚህም በዞኑ ሁሉንም ወረዳዎች የኤሌክትሪክ ሀይል ተደራሽ ማድረግ የተቻለ ሲሆን፣ ጥያቄ ሲነሳባቸው የነበሩ ቀበሌዎችንም የአገልግሎቱ ተጠቃሚ የማድረግ ሥራ በስፋት መሠራቱን ነው ያብራሩት። ከዚህ በተጨማሪም በዞኑ የማሰራጫ ጣቢያዎችን ቁጥር 21 በማድረስ የመብራት መቆራረጥን ለመቅረፍ የተሠራው ሥራም ውጤታማ እየሆነ ነው ብለዋል። ያረጁ ምሰሶዎችን የማደስ እና በኮንክሪት የመተካት ሥራ መሠራቱን የገለጹት አቶ ሲሳይ፣ በዚህ ዓመት የኃይል መቆራረጥን ለመቀነስ ከ50 በላይ ተጨማሪ ትራንስፎርመሮች መተከላቸውን አብራርተዋል። ከዚህ በተጨማሪም ዘመናዊ ቆጣሪዎችን ለነዋሪዎች በማቅረብ አጠቃላይ አገልግሎቱን ዲጂታላይዝ የማድረግ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል። በዚህ ወር መጨረሻም የዘንድሮውን የኤሌክትሪክ ተጠቃሚዎች ቁጥር ወደ 15 ሺህ ከፍ ለማድረግ በትኩረት እየሠራን ነው ብለዋል። የጅማ ዞን ጎማ ወረዳ ጂማቴ ደሩ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አባነጋ ኃጂ ከዚህ ቀደም በአካባቢያቸው መብራት ተደራሽ ባለመሆኑ ሲቸገሩ መቆየታቸውን ገልጸው ፣ለዘመናት የነበረው ጥያቄያችን አሁን ተፈቷል ብለዋል። ሌላኛው የጅማ ከተማ በቾ ቦሬ ቀበሌ ነዋሪዎች ካሊድ ዛኪር እና መሐመድሳሊህ ሀቢብ፣ ዘንድሮ ተጨማሪ ትራንስፎርመር በመተከሉ ከዚህ ቀደም የነበረው መቆራረጥ በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል ብለዋል።
በዞኑ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የዓሳ ዕርባታ ስራ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነትን እያሳደገ ነው
Jun 11, 2026 92
ደብረ ብርሃን ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፡- በሰሜን ሸዋ ዞን በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የዓሳ ዕርባታ ስራ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነትን እያሳደገ መሆኑ ተገለጸ። በዞኑ በዓሳ ልማቱም 1 ሺህ 374 አርሶ አደሮች እየተሳተፉ እንደሚገኝም ተገልጿል። በዞኑ እንስሳትና ዓሳ ሀብት መምሪያ የዓሳ ልማት አስተዳደር ባለሙያ ወይዘሮ እማዋይሽ የኋላ እሸት እንዳሉት የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር በዓሳ ልማት ዘርፍ ምርታማነትን እና የተሳታፊዎችን ቁጥር እያሳደገ ነው። በመርሃ ግብሩ ወጣቶች፣ ሴቶችን እና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በወንዞች ላይ ብቻ ተወስኖ የነበረን የዓሳ እርባታ ስራ በመርሃ ግብሩ በአርሶ አደሮች ጓሮ በተዘጋጁ ኩሬዎች እንዲከናወን በመደረጉ የዓሳ ምርታማነት ጨምሯል ብለዋል። በዚህም የዓሳ ዕርባታ ስራው በኩሬዎችና በወንዞች ላይ በስፋት እየተከናወነ መሆኑንም ተናግረዋል። ይህም ራስን በምግብ ለመቻል የሚደረገውን ጥረት ከመደገፍ ባለፈ ዓሳን በመመገብ ነፍሰ ጡር እናቶችና ህፃናት ጤንነታቸውን እንዲጠብቁ ማስቻሉንም አክለዋል። አርሶ አደሩ ዓሳን ለቤት ውስጥ ፍጆታው ከመጠቀም ባሻገር ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን እያሳደገ መምጣቱን ገልፀዋል። በዓሳ ልማቱም 1 ሺህ 374 አርሶ አደሮች እየተሳተፉ እንደሚገኝ ገልጸው እስካሁን በተደረገ እንቅስቃሴም 26 ሺህ 364 የዓሳ ጫጩቶች በኩሬዎች እንዲራቡ በመደረግ ላይ መሆኑንም አስረድተዋል። በባሶና ወራና ወረዳ የዲቡት ቀበሌ አርሶ አደር ታደሰ ማሞ እንዳሉት የዓሳ ምርታማነትን ለማሳደግ የተጀመረው ጥረት ስርዓተ ምግብን ከማሻሻል ባሻገር ተጨማሪ ገቢ እንድናገኝ አስችሎናል። በቀጣይ ከወረዳው አስተዳደር ጋር በመቀናጀት ተጨማሪ የዓሳ ጫጩቶችን በማምጣት የተሻለ ምርት ለማምረት ማቀዳቸውንም አክለዋል።
የትምህርት ሥርዓትን ከገበያ ፍላጎት ጋር ማጣጣም ዘላቂ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ ነው
Jun 11, 2026 141
አዲስ አበባ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦የትምህርት ሥርዓትን ከገበያ ፍላጎት ጋር ማጣጣም ዘላቂ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምክትል ዋና ጸሀፊ አሚና መሐመድ ገለጹ። በሥራ ፈጠራ ላይ ትኩረቱን ያደረገ የአፍሪካ ዴቨሎፕመንት ኢምፓክት ፎረም 2026 በተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ECA) መካሄድ ጀምሯል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምክትል ዋና ጸሀፊ አሚና መሐመድ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ አፍሪካ ታላላቅ ተግዳሮቶችና መልካም አጋጣሚዎች ባሉበት ወሳኝ መስቀለኛ መንገድ ላይ ትገኛለች፡፡ በዚህ ወቅት ጥራትና ዘላቂነት ያላቸው የሥራ ዕድሎችን ለመፍጠር ዘመናዊ የትምህርት ሥርዓቶችን ከገበያው ትክክለኛ ፍላጎት ጋር ማጣጣም እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በተለይም በፍጥነት እያደገ የመጣውን የአፍሪካ ወጣት ቁጥር ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ጥራት ያላቸው የሥራ ዕድሎችን መፍጠር አፋጣኝ ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ሊሆን እንደሚገባ አሳስበዋል። ባለፉት ዓመታት ከአምራች ኢንዱስትሪ መስፋፋት እስከ ወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራና የክህሎት ልማት ያሉ የአፍሪካን አንገብጋቢ ተግዳሮቶች ለመፍታት ከመንግሥታት፣ ከቀጣናዊ ተቋማትና ከግል ዘርፉ ጋር በጋራ ሲሠራ መቆየቱን አስታውሰዋል። ከዚህ የጋራ ሥራም ትልቅ ትምህርት መገኘቱን ጠቅሰው፣ምርምር፣መረጃና ማስረጃዎች ብቻቸውን ለውጥ አያመጡም፤ ከንግግርና ከሪፖርት ባለፈም ወደ ተግባራዊ እርምጃ መግባት አማራጭ የሌለው ጉዳይ ነው ብለዋል። የስራ ዕድሎችን መፍጠር በመንግሥታት ብቻ ሊሳካ እንደማይችል ጠቁመው፤ይህም የፖሊሲ አውጪዎችን፣ ተመራማሪዎችን፣ የልማት አጋሮችንና የግል ዘርፉን በአንድ ላይ የሚያገናኝ ንቁ ሥነ-ምሕዳርን እንደሚጠይቅ አስረድተዋል። የዘንድሮው ፎረም መፍትሔዎችን ለመለየት፣ጠንካራ አጋርነትን ለመገንባትና ተግባራዊ የመድረሻ መንገዶችን ለመንደፍ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን በአንድ ላይ ያገናኘ ሲሆን፣ከውይይት ባለፈ በመላው አፍሪካ ላሉ ወጣቶች ወደ ተጨባጭ ውጤት የሚቀይሩ ትርጉም ያላቸው ተግባራት እንደሚጠበቁበት ተመላክቷል።
በዞኑ በመኸር እርሻ ከ16 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ግብ ተይዞ የማሳ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Jun 11, 2026 142
ጊምቢ፤ ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ):-በምዕራብ ወለጋ ዞን በዘንድሮ የመኸር እርሻ ከ16 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት ግብ ተይዞ የማሳ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፈይሳ ሀምቢሳ ለኢዜአ እንደገለጹት በ2018/19 የመኸር ወቅት ከ484 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ በተለያዩ ሰብሎች ለማልማት ታቅዶ እየተሰራ ነው። ዕቅዱን ለማሳካትም የተቀናጀ የግብርና ሥራ መጀመሩን ገልጸው፣ እስካሁን በተደረገ ጥረት 155 ሺህ 322 ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለመሸፈን መቻሉን ተናግረዋል። ቀሪውን መሬት በተደጋጋሚ በማረስ ለዘር እየተዘጋጀ መሆኑን ገልጸው፣ በምርት ዘመኑ ለሜካናይዜሽን እርሻም ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። ውጤታማ የግብርና ሥራ ለማከናወንም በዞኑ 28 የእርሻ ትራክተሮች ሥራ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለልማቱ እስካሁን ድረስ 116 ሺህ ኩንታል የሚጠጋ የአፈር ማዳበሪያ የተሰራጨ ሲሆን ከዚህ በተጓዳኝ አርሶ አደሩ የተፈጥሮ ማዳበሪያ በስፋት አዘጋጅቶ እንዲጠቀም እየተደረገ መሆኑን አቶ ፈይሳ ተናግረዋል። የመኸር እርሻን ውጤታማ ለማድረግም ለማልማት ከታቀደው መሬት ውስጥ አብዛኛው መሬት በኩታ ገጠም አሰራር እንዲለማ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ በልማቱ እየተሳተፉ ካሉ የበጊ ወረዳ አርሶ አደሮች መካከል አቶ ዳዊት ታሲሳ በሰጡት አስተያየት፤ ባለፈው ዓመት የመኸር እርሻ ከአንድ ሄክታር መሬት 26 ኩንታል የበቆሎ ምርት ማግኘታቸውን አስታውሰዋል። ዘንድሮ ከሄክታር እስከ 34 ኩንታል የበቆሎ ምርት ለማግኘት ማቀዳቸውን ገልጸው ለእዚህም ማሳቸውን ደጋግመው በማረስና በማለስለስ በዘር እየሸፈኑ መሆናቸውን ተናግረዋል። ውጤታማ ልማት እንዲያከናውኑ የአፈር ማዳበሪያ በጊዜ ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ የእዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ከማል ቦካ ናቸው። ያዘጋጁትን የተፈጥሮ ማዳበሪያ በእርሻ ማሳቸው ላይ በመበተንና በማዋሃድ ምርታማነታቸውን ለማሳደግ ተግተው እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። ባላቸው አንድ ሄክታር የሚጠጋ መሬት ላይ በቆሎና ስንዴ በማልማት ከ32 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት አቅደው እየሰሩ መሆኑንም አመልክተዋል። የበጊ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ወቅጋሪ ከበደ በበኩላቸው፣ በወረዳው በዘንድሮው የመኽር ወቅት 44 ሺህ 930 ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች እንደሚለማ ተናግረዋል። የአርሶ አደሩ የግብርና ቴክኖሎጂ አጠቃቀም እየተሻሻለ በመምጣቱ በዘንድሮው የመኸር አዝመራ አብዛኛው መሬት በኩታ ገጠም ለማልማት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ለመኸር እርሻው የሰብል ልማት ስራው እስካሁን ድረስ 4ሺህ 389 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱንም አስታውቀዋል።
በክልሉ የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጡና ገበያን የሚያረጋጉ የግብርና ልማት ስራዎች ይጠናከራሉ
Jun 11, 2026 156
ሃዋሳ፤ ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ) ፡-በሲዳማ ክልል በክልሉ የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጡና ገበያን የሚያረጋጉ የግብርና ልማት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። የሲዳማ ክልል አቀፍ የመኸር እርሻ ንቅናቄ መድረክ በሃዋሳ እየተካሄደ ነው። የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በዚህ ወቅት እንደገለጹት በክልሉ የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጡና ገበያን የሚያረጋጉ የግብርና ልማት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። ለዚህም ባለፉት ዓመታት ጦሙን የሚያድር መሬት እንዳይኖር የጋራ መግባባት ተፈጥሮ በተሰራው ስራ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸው በተያዘው የምርት ዘመንም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የግብርና ምርታማነቱን ለማሳካትም ከበልግ ምርቱ መሰብሰብ ጎን ለጎን የመኸር ሰብልን ውጤታማ ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። በዚህም የቤተሰብ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ትርፍ አምርቶ ገበያን ለማረጋጋትና የኑሮ ውድነትቱን ተፅዕኖ ለመቀነስ ለሚያስችሉ የግብርና ልማት ስራዎች ትኩረት እንደሚሰጥ ተናግረዋል። በምርት ዘመኑ የተያዘውን እቅድ ለማሳካትም በየደረጃው ያለ አመራር የህብረተሰቡን አቅም በማስተባበር ለውጤቱ በትጋት መስራት እንዳለበትም አሳስበዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው በዘንድሮው መኸር ከ169 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ሰብሎች ይለማል ብለዋል። በዚህም ከ16 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ ጠቅሰው ለዚህም በየደረጃው ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል። የዛሬው መድረክ አላማም አመራሩ በእቅዱ ላይ የጋራ መግባባት ፈጥሮ ወደ ተግባር እንዲገባ የሚያደርግ ነው ብለዋል። በመድረኩ ለመኸር ወቅት የተዘጋጀ ዝርዝር እቅድ ቀርቦ ውይይት እየተደረገበት ነው።
የኢትዮጵያ የተቀናጀ የገንዘብና የፊሲካል ፖሊሲ ውጤታማ የኢኮኖሚ አስተዳደርን በማስፈን ፈጣን ዕድገት እንዲመዘገብ አስችሏል
Jun 11, 2026 142
አዲስ አበባ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የተቀናጀ የገንዘብና የፊሲካል ፖሊሲ ውጤታማ የኢኮኖሚ አስተዳደርን በማስፈን ፈጣን ዕድገት እንዲመዘገብ ማስቻሉን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ ገለጹ። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመኑ 25ኛ መደበኛ ስብሰባውን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ የፌዴራል መንግሥት የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀትን በተመለከተ በሚያቀርቡት የበጀት መግለጫ ላይ እየተወያየ ይገኛል። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ በመግለጫቸው፤በሚኒስትሮች ምክር ቤት የቀረበውን የፌዴራል መንግሥት የ2019 ዓ.ም በጀት ዓመት ረቂቅ በጀትን አስመልክቶ መግለጫ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ጉዞና የተያዘው በጀት ዓመት የኢኮኖሚ ዕይታና አፈፃጸም በማመላከት ተደግፎ የቀረበውን የቀጣይ በጀት ዓመት የበጀት ድልድል የተመሰረተባቸውን ታሳቢዎች በዝርዝር አቅርበዋል። የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያና የአስር ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ ስኬታማ ትግበራ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ውስጣዊና ውጫዊ ጫናዎችን በብቃት በመቋቋም ጠንካራ አፈጻጸምና ውጤት ማስመዝገቡን ገልጸዋል። በዚህም ከ2012 እስከ 2016 ባሉት ዓመታት የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በአማካይ በየዓመቱ የ6 ነጥብ 8 በመቶ ዕድገት ያስመዘገበ ሲሆን፤ በ2017 ደግሞ የ9 ነጥብ 2 በመቶ አስደናቂ ዕድገት አስመዝግቧል ብለዋል። በተያዘው በጀት ዓመትም ከመካከለኛው ምሥራቅ የመነጩ ጫናዎችንም ጭምር በመቋቋም የ10 ነጥብ 2 በመቶ የኢኮኖሚ ዕድገት እንደሚመዘገብ አስታውቀዋል። ይህም በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያን ፈጣን ኢኮኖሚ እያስመዘገቡ ከሚገኙ የዓለም ሀገራት መካከል በግንባር ቀደምትነት የሚያሰልፋት ስኬታማ የዕድገት ጉዞ ላይ መሆኗን እንደሚያሳይ አንስተዋል። በኢትዮጵያ ፈጣን የዕድገት ጉዞም የዋጋ ንረትን በመግታት ስኬታማ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲዎችን በመተግበርና ምርታማነትን በማሳደግ የመጣ መሆኑን ልዩ እንደሚያደርገው አስረድተዋል። የተቀናጀ የገንዘብና የፊሲካል ፖሊሲ ትግበራ፣ የምርታማነት በማሻሻልና ጠንካራ የኢኮኖሚ ዕድገት በማስመዝገብ የዋጋ ግሽበትን በተሳካ ሁኔታ መቀነስ መቻሉን ገልጸዋል። የተወሰዱ እርምጃዎችም ሸቀጦችና የአገልግሎቶች የዋጋ ግሽበት ወደ ነጠላ አሃዝ በማውረድ አዎንታዊ ውጤት ማስገኘቱን አስታውቀዋል። በግብርና ዘርፍም በሰብልና እንስሳት ምርት አቅርቦት ሰንሰለት ውጤታማነት በማሳደግና የከተማ ግብርናን በማበረታታት የዋጋ ንረትን በመቀነስ ለዜጎች እፎይታን በመፍጠር ወሳኝ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። በባንኮች የሚሰጡ አጠቃላይ የሀገር ውስጥ ብድር የተገደበ ዕድገት እንዲኖረው በማድረግ የገንዘብ አቅርቦቱ ከኢኮኖሚ ዕድገት ጋር የተጣጣመ እንዲሆን መደረጉ የዋጋ ንረትን እንዲቀንስ ማድረጉን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ለበጀት ጉድለት መሸፈኛ የሚወሰድ ሙሉ ለሙሉ እንዲቆም መደረጉ የዋጋ ንረትን ወደ ነጠላ አሃዝ በማውረድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ማበርከቱን አንስተዋል። በዚህም በነሐሴ 2014 ዓ.ም ወደ 34 ነጥብ 5 በመቶ አሻቅቦ የነበረውን አጠቃላይ የዋጋ ንረት በመጋቢት 2016 ዓ.ም ወደ 9 ነጥብ 4 በመቶ ነጠላ አሃዝ ዕድገት ማውረድ መቻሉን አስታውቀዋል። በበጀት ዓመቱም የኢትዮጵያ ስታስቲስክስ በየወሩ በሚያወጣው የሸማቾች ዋጋ ኢንዴክስ መሰረት ምግብ ነክ እና ምግብ ነክ ያልሆኑ ሸቀጦች ዋጋ ላይ የታየው ቅናሽ አዎንታዊ ውጤቱን በግልፅ እንደሚያሳይ አስረድተዋል። የውጭ ምንዛሬ ለውጡም የዋጋ ንረትን እንዳያባብስ ቀድሞውኑ የተቀናጀ ስራ በመስራት የዋጋ ንረትን በከፍተኛ ደረጃ መቆጣጠር የተቻለበት መሆኑን ጠቅሰዋል። ይህም ይበልጥ የተረጋጋና የበለጸገ ኢኮኖሚን ለመገንባት የሚደረገውን ጉዞ የሚያጠናክር ታላቅ ምዕራፍ መሆኑን ጠቁመዋል።
የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት ከ2 ነጥብ 339 ትሪሊየን ብር በላይ ሆኖ ቀረበ
Jun 11, 2026 146
አዲስ አበባ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦የፌዴራል መንግሥት የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት ከ2 ነጥብ 339 ትሪሊየን ብር በላይ ሆኖ ቀርቧል። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛ ዓመት የሥራ ዘመኑ 25ኛ መደበኛ ስብሰባውን የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ የፌዴራል መንግሥት የ2019 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀትን በተመለከተ በሚያቀርቡት የበጀት መግለጫ ላይ እየተወያየ ነው። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ በመግለጫቸው፤ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የቀረበውን የፌዴራል መንግሥት የ2019 ዓ.ም በጀት ዓመት ረቂቅ በጀትን አስመልክቶ መግለጫ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ጉዞና በመገባደድ ላይ ያለውን በጀት ዓመት የኢኮኖሚ ዕይታና አፈፃጸም በማመላከት ተደግፎ የቀረበውን የቀጣይ በጀት ዓመት የበጀት ድልድል የተመሰረተባቸውን ታሳቢዎች በዝርዝር አቅርበዋል። የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሺዴ የረቂቅ በጀቱን መግለጫ ለምክር ቤቱ ባቀረቡበት ወቅት እንዳሉት፥ በጀቱ መንግሥት የያዛቸውን የልማትና የማክሮ ኢኮኖሚ ዕቅዶች ታሳቢ በማድረግ የተዘጋጀ ነው። ለ2019 በጀት ዓመት ከቀረበው በጀት ውስጥ 1 ነጥብ 236 ትሪሊየን ብር ለመደበኛ ወጪ፣ 568 ነጥብ 2 ቢሊየን ብር ለካፒታል ወጪ እንደሚውል አስረድተዋል። በተጨማሪም 520 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር ለብሔራዊ ክልላዊ መንግስታት የበጀት ድጋፍ እንዲሁም 14 ቢሊየን ብር ለክልሎች የዘላቂ ልማት ግብ ማስፈጸሚያ ይውላል ነው ያሉት። ከአጠቃላይ በጀቱ ውስጥ 52 ነጥብ 9 በመቶ የሚሆነው ከፍተኛ በጀት ለመደበኛ ወጪ የተመደበ መሆኑን ገልጸው፥ ከዚህም ውስጥ 542 ቢሊየን ብር ለሀገር ውስጥ እና ለውጭ የእዳ ክፍያ እንደሚውል ጠቁመዋል። በተጨማሪም ከዚሁ የመደበኛ ወጪ ውስጥ 236 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር ለማዳበሪያ፣ ለነዳጅ ድጎማ እንዲሁም የኢትዮጵያ ነዳጅ ድርጅትን ካፒታል ለማሳደግ የተመደበ ነው ብለዋል። ለመንግስት ባለበጀት መስሪያ ቤቶች ለደመወዝ፣ ለአበልና ልዩ ልዩ ክፍያዎች 170 ነጥብ 8 ቢሊየን ብር መመደቡን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በ2019 በጀት ዓመት 10 ነጥብ 1 በመቶ እድገት እንደሚያስመዘግብ ይጠበቃል ነው ያሉት። የመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በኢኮኖሚ እድገቱ ላይ ተጽዕኖ እንደሚያሳድር አመላካች ሁኔታዎች መኖራቸውን ገልጸዋል። በተጨማሪም የ2019 በጀት የመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት የሚያሳድረውን ተጽእኖ ከግምት በማስገባት መዘጋጀቱን አስረድተዋል። በ2019 በጀት ዓመት የፌደራል መንግስት ጠቅላላ ገቢ 1 ነጥብ 817 ትሪሊየን ብር እንደሚሆን ግምት ተወስዷል ብለዋል። ከዚህም ውስጥም 1 ነጥብ 6 ትሪሊየን ብር ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ገቢዎች እንደሚሰበሰብ መታቀዱን አመልክተዋል። ለ2019 በጀት ዓመት የቀረበው 2 ነጥብ 339 ትሪሊየን ብር በጀት ከዘንድሮው በጀት ዓመት አንጻር የ21 ነጥብ 3 በመቶ እድገት እንዳለው ተናግረዋል።
በአዲስ አበባ አዲሱ የተሽከርካሪ ሠሌዳ መሰጠት ተጀመረ
Jun 11, 2026 147
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ አዲሱ የተሽከርካሪ ሠሌዳ መሰጠት መጀመሩን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አሽከርካሪና ተሽከርካሪ ፍቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን አስታወቀ፡፡ የባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ዘገየ በላይነህ በሰጡት መግለጫ፤ አዲሱ የተሽከርካሪ ሠሌዳ ከዛሬ ጀምሮ መሰጠት መጀመሩን ይፋ አድርገዋል፡፡ አዲሱ የተሽከርካሪ ሠሌዳ ሀገራዊ ይዘትን የተላበሰ፣ ተመሳስሎ መሠራት እንዳይቻል ሆኖ የተዘጋጀ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ባለሥልጣኑ አገልግሎቱን ለማዘመንና ቁጥጥሩን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ የተለያዩ ሥራዎችን እየሠራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። ለዚህም አዲሱን የተሽከርካሪ ሠሌዳ አጠቃላይ ይዘትና አተገባበር ከበፊቱ በተሻለ መልኩ ሥራዎችን ለማዘመን፣እንዲሁም ኢትዮጵያን የሚገልጹ መለያዎችን የያዘ እና ዓለም አቀፍ መስፈርቱን የተከተለ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ አዲሱ ሠሌዳ ከዚህ በፊት በሌላ መልኩ ማኅበራዊ መስተጋብርን በማጠናከር እና የሀብት ብክነትን የመከላከል ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ መኖሩን ገልጸዋል። አዲሱ ሠሌዳ ከዛሬ ቀን ጀምሮ መሰጠት እንደሚጀምር ጠቅሰው፣ሠሌዳው የተለያዩ መረጃዎችን የሚይዝ በመሆኑ ለሕግ ማስከበር ሥራ የሚመች፣ ቶሎ የማይበላሽ እና ወጪ ቆጣቢ መሆኑን አብራርተዋል። ሠሌዳው ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ መሰጠት መጀመሩን እና ተገልጋዮች በተመዘገቡበት ቅደም-ተከተል እንደሚወስዱ፤በክልል ከተሞች ደግሞ በቅርቡ እንደሚጀምር ተገልጿል።
ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር በመሰለፍ በብሄራዊ ጥቅሟ ላይ ክህደት የሚፈፅሙ ባንዳዎችን መታገል ሀገራዊ ግዴታችን ነው-የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች
Jun 11, 2026 112
ደሴ፤ሰኔ 4/2018 (ኢዜአ)፡-ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር በመሰለፍ በብሄራዊ ጥቅሟና ክብሯ ላይ ክህደት የሚፈፅሙ ባንዳዎችን መታገል ሀገራዊ ግዴታችን ነው ሲሉ የተለያዩ ተፎካካሪ ፓርቲ አመራሮች ገለጹ። ኢትዮጵያ ከሀገራት ጋር በትብብር በመስራት ብሄራዊ ጥቅሟን የማስከበርና ህልውናዋን የማስጠበቅ ዲፕሎማሲያዊ ጥረቷን አጠናክራ ቀጥላለች። የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄዋ ምላሽ እንዲያገኝ በታሪክ፣ በመልክአ ምድር እንዲሁም በዓለም አቀፍ ህግ መሰረት እየሰራች መሆኑ ይታወቃል። በመሆኑም የባህር በር ጥያቄና ሌሎችም የሀገር ብሄራዊ ጥቅሞች የትውልዱ ጉዳይ ሆነው ተጠናክረው የቀጠሉ አጀንዳዎች ናቸው። ይሁን እንጂ የሀገርን ብሄራዊ ጥቅም፣ክብርና ሉአላዊነት በመፃረር ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር በማበር በባንዳነት የተሰለፉ መኖራቸው የሚታይ እውነታ ሆኗል። በዚሁ ጉዳይ ላይ የኢዜአ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የተለያዩ ተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች ከኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር በመሰለፍ በብሄራዊ ጥቅሟና ክብሯ ላይ ክህደት የሚፈፅሙ ባንዳዎችን መታገል ሀገራዊ ግደታችን ነው ሲሉ ተናግረዋል። የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) የደቡብ ወሎ ዞንና ደሴ ከተማ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ከድር ይመር፤ የሀገር ሰላም፣ ሉዓላዊነትና ብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ ለማንም ቢሆን ለድርድር የማይቀርብ የሀገር ህልውና ጉዳይ ነው ብለዋል። በመሆኑም ከዚህ በተቃራኒ ከጠላት ጋር የሚቆም የፖለቲካ ፓርቲ፣ ግለሰብም ሆነ ሌላ አካል ካለ የሀገሩን ጥቅም አሳልፎ እየሰጠ ስለመሆኑ ግልጽ መሆኑን አንስተዋል። ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም፣ልማት፣ ብሄራዊ ጥቅምና ሉዓላዊነት መከበር ፓርቲያቸው የጸና አቋም ያለው መሆኑን አንስተው፥ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ እንሰራለን ብለዋል። የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የደቡብ ወሎና ደሴ ከተማ ቅርጫፍ ጽህፈት ቤት የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ሻምበል ደምሌ ተረፈ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች የሃሳብ ልዩነት ቢኖረንም በሀገር ሉአላዊነትና ብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ ላይ ልዩነት የለንም ብለዋል። በመሆኑም ለኢትዮጵያ ሰላም፣ልማትና ለብሄራዊ ጥቅሟ መከበር የዜግነት ግዴታችንን ለመወጣት እንሰራለን ሲሉ ተናግረዋል። የነጻነትና እኩልነት ፓርቲ የደቡብ ወሎ ዞንና ደሴ ከተማ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አያሌው አሸብር፤ፓርቲያችን በሀገር ሉአላዊነትና ብሄራዊ ጥቅም ጉዳይ ጠንካራ አቋም ይዞ እየሰራ ይገኛል፤ በቀጣይም አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በኢትዮጵያና ህዝቦቿ ላይ የውስጥና የውጪ ጠላቶች የሚያደርጉትን ማናቸውም የጥፋት እንቅስቃሴ የማንቀበለውና የምንታገለው ይሆናል ሲሉ ተናግረዋል።
መንግስታዊ አገልግሎት አሰጣጥ ወደ ህዝቡ በመቅረቡ የመሰረተ ልማት ችግሮች በህዝብ ተሳትፎ ለመፍታት እያስቻለ ነው
Jun 11, 2026 152
ሮቤ፣ ሰኔ 4 /2018 (ኢዜአ):- በባሌ ዞን መንግስታዊ አገልግሎት አሰጣጥ ይበልጥ ወደ ህዝቡ በመቅረቡ የመሰረተ ልማት ችግሮች በህዝብ ተሳትፎ ለመፍታት እያስቻለ መሆኑን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ዓመታት አዲስ የቀበሌ አደረጃጀት ተዘርግቶ ህዝቡ መንግስታዊ አገልግሎቶችን በቅርበት እያገኘ መሆኑ ይታወቃል። በባሌ ዞን የተዘረጋው የቀበሌ አደረጃጀትም የህዝብን የልማት ተሳትፎ በማሳደግ የመሰረተ ልማት ችግሮች በህብረተሰቡ ተሳትፎ እንዲፈቱ ዕድል መፍጠሩን የዞኑ አስተዳደር ገልጿል። በብልጽግና ፓርቲ የዞኑ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ብርሃኑ አፍራሳ እንደገለጹት፤ የቀበሌ አደረጃጀቱ የህብረተሰቡን የልማት ተሳትፎ በማሳደግ የመሰረተ ልማት ችግሮች እንዲፈቱ ዕድል እየፈጠረ ነው። ይህ አደረጃጀት የህብረተሰቡን የመልካም አስተዳደር፣ የአገልግሎትና የልማት ጥያቄዎችን በቅርበት ለመመለስ ትልቅ እገዛ እያደረገ መሆኑንም አክለዋል። ከዚህ በፊት ህብረተሰቡ ከፍትህና ከሌሎች ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን ለማስጨረስ ወደ ወረዳና ዞን ማዕከላት በመመላለስ ለአላስፈላጊ ወጪና ለስራ ጊዜ መባከን ይዳረግ ነበር ያሉት ኃላፊው፤ በአዲሱ አደረጃጀት እነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ ከማግኘታቸውም በላይ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎችን ለማፋጠን ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ተናግረዋል። በዚህም በህዝብ ተሳትፎ እንዲሁም በመንግስት አቅም የቀበሌ ጽሕፈት ቤቶች ግንባታን ጨምሮ የትምህርት ቤቶች፣ የመንገድና የድልድይ መሰረተ ልማቶች እየተገነቡ መሆኑን በአብነት አንስተዋል። የሀረና ቡሉቅ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ኢብራሂም ሀሰን በበኩላቸው፤ አዲሱ አደረጃጀት የወረዳውን ህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በቅርበት ለመመለስ እያገዘ መሆኑን ገልጸዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በህዝቡ ተሳትፎ የተሰሩ የድልድይ፣ የመንገድ፣ ሼዶችና የቀበሌ ጽህፈት ቤቶች ግንባታ ሥራዎችም የአደረጃጀቱ ውጤቶች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡ የወረዳው ነዋሪዎች መካከል አቶ በከር ሱልጣን፤ የቀበሌ አደረጃጀቱ የአካባቢውን ህብረተሰብ የመልካም አስተዳደርና የልማት ጥያቄዎች በቅርበት እንዲመለሱ እያገዘ መሆኑን ገልጸው፣ በህዝብ ተሳትፎ የተገነቡትን ድልድይና የወጣቶች መስሪያ ሼድ በምሳሌነት ጠቅሰዋል። ሌላው የወረዳው ነዋሪ አቶ አህመድ መሐመድ በበኩላቸው፤ የቀበሌ አደረጃጀቱ በአካባቢያቸው ተግባራዊ መደረጉ ከዚህ በፊት መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማግኘት ይደርስባቸው የነበረውን እንግልት ያስቀረና በልማት ላይ የሚያደርጉትን ተሳትፎ ያሳደገ መሆኑን ተናግረዋል። በባሌ ዞን በአጠቃላይ 189 አዲስ የተደራጁ ቀበሌዎች የሚገኙ ሲሆን፣ በእነዚህ ቀበሌዎች የተሟላ የሰው ኃይል ተመድቦ ለማህበረሰቡ በቅርበት አገልግሎት እየተሰጠ እንደሚገኝ ታውቋል።
ረቂቅ አዋጁ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮችን ወደ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ እና ገበያ መር ሥርዓት ለማሸጋገር ጉልህ አስተዋጽኦ ይኖረዋል
Jun 10, 2026 1068
አዲስ አበባ፤ሰኔ 3/2018 (ኢዜአ)፦የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮችን ወደ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ እና ገበያ መር ሥርዓት ለማሸጋገር ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት የፖለሲና የምግብ ስርዓትና ጥናት ሲኒየር ዳይሬክተር ረታ ዋጋሪ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አምራቾች በኩባንያ በማደራጀት፣ መሬት የመጠቀም መብታቸውን፣ የእንስሳት ሀብታቸውንና ጉልበታቸውን ወደ ካፒታል በመለወጥ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የሚያስችል ግልጽ የሕግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ ረቂቅ አዋጁ መዘጋጀቱን አብራርተዋል። ረቂቅ አዋጁ በርካታ ዓላማዎች ያካተተ መሆኑን የጠቀሱት ዳይሬክተሩ ለዘርፉ ዕድገት ምቹ የሆነ ግልጽ አሠራር መዘርጋት፣ አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አምራቾች ወደ መካከለኛ አልሚነት በመሻገር ኑሮአቸውን እንዲያሻሽሉ ማስቻል እንዲሁም ለገጠር ትራንስፎርሜሽን እውን መሆን የጎላ አስተዋጽኦ ማድረግ የሚሉ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል፡፡ አዋጁ ለአነስተኛ ይዞታ አምራቾች የፋይናንስ እና የኢንሹራንስ ተደራሽነትን በማመቻቸት፣ ከዘመናዊ አሠራርና አገልግሎቶች ተጠቃሚ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የግብርና ቢዝነስ ኩባንያዎች የማቋቋሚያ ካፒታል፣ የአባላት ምዝገባ ፣ የኩባንያዎች አደረጃጀት ፣ የተቋማት ስልጣንና ተግባር የሕግ ተጠያቂነትና ሌሎች ጥያቄዎች ከቋሚ ኮሚቴው አባላት ተነስተዋል። በግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት አማካሪ አቶ ሽመክት ማሩ በሰጡት ማብራሪያ፤ በረቂቅ አዋጁ ላይ የተቀመጡት የኩባንያዎች መሥራች አባላት ቁጥር እና የማቋቋሚያ መነሻ ካፒታል መስፈርቶች መካተታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ መስፈርቶቹ ባለፉት ዓመታት በሀገሪቱ የግብርና ዘርፍ ከተገኙ ልምዶች፣ ከዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችና ጥልቅ ጥናቶች ላይ ተመስርተው የተቀረጹ መሆናቸውን አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሤ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ የተዘጋጀበት ዋና ዓላማ የግብርና ግብዓትና ቴክኖሎጂ አቅርቦትን በማሳለጥና ተደራሽ በማድረግ የአነስተኛ ይዞታ አምራቾችን ምርት፣ ምርታማነትና ገቢ ለማሳደግ መሆኑን አንስተዋል። አዋጁ የግብርና ምርትን በከፍተኛ መጠንና ጥራት በማሰባሰብ፣ የግብይትና የእሴት ጭመራ ተግባራትን በማዘመን ረገድ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ይህ መሆኑ የአነስተኛ ይዞታ አምራቾችን የኑሮ ደረጃ ከማሻሻሉም በላይ ለሀገሪቱ አጠቃላይ ኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ያሰችላቸዋል ብለዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሰለሞን ላሌ፤ ረቂቅ አዋጁ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮችን በግብርና ቢዝነስ ኩባንያ በማደራጀትና በማቀናጀት፣ ምርታማነትን ለማጎልበትና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡ አዋጁ በግብርናው ዘርፍ የእሴት ጭመራን ለማምጣት እንዲሁም ወደ ውጭ የሚላኩ ምርቶችን በማሳደግ የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማጎልበት እንደሚያስችል ጠቅሰዋል።
የታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የታክስ አሰራርን በማዘመን ፍትሐዊነትና የሕግ ተገዢነትን ለማረጋገጥ እገዛ ያደርጋል
Jun 10, 2026 902
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2018 (ኢዜአ)፡- የታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ የታክስ አሰራርን በማዘመን ፍትሐዊነትና የሕግ ተገዢነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ እገዛ እንደሚያደርግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የታክስ አስተዳደር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር የአስረጂ መድረክ ተካሂዷል። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ፍቃዱ ሆረታ በዚህ ወቅት፤ የታክስ አስተዳደር ረቂቅ አዋጅ ከኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ጋር የተጣጣመ ዘመናዊ የታክስ አሰራር ለመፍጠር ያስቻላል ብለዋል። በታክስ ከፋዩ ማህበረሰቡ የሚነሱ መሰረታዊ የፍትሐዊና የመልካም አስተዳደር ቅሬታዎችንም መፍትሔ ለመስጠት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ገልጸዋል። የመንግሥትን ገቢ የመሰብሰብ አቅም በማጎልበት ተጠያቂነትን ከግልጸኝነት ያጣመረ ዘመናዊ የአሰራር ሥርዓት መዘርጋት እንደሚያስችልም ተናግረዋል። የምክር ቤቱ አባላትና የሕግ ማዕከል ባለሙያዎችም፤ በማሻሻያ ረቂቅ አዋጁ የታክስ ስሌት፣ የይርጋ ጊዜ ገደብ፣ የታክስ ከፋይ መስተንግዶና ተያያዥ ጉዳዮችን በማስመልከት ጥያቄ አንስተዋል። በገንዘብ ሚኒስቴር ከፍተኛ የሕግ አማካሪ ዋሲሁን አባተ፤ በረቂቅ አዋጁ የይርጋ ጊዜው አስር ዓመት ሆኖ መቀመጡ በታክስ ከፋዩ ላይ የሚኖረውን ጫና መቀነስ እንደሚያስችል ተናግረዋል። በገንዘብ ሚኒስቴር የሕግ ጉዳዮች መምሪያ ኃላፈ ተወዳጅ መሐመድ፤ የታክስ ደረሰኝ አለመስጠት ተመሳሳይ የገንዘብ ቅጣት መጣሉ ሆን ተብሎ የሚፈጸምን የታክስ ማጭበርበር በማስቀረትና ደረሰኝ መቁረጥን ባህል ያደርጋል ብለዋል። በገቢዎች ሚኒስቴር የታክስ አማካሪ ያሬድ ፍቃደ በበኩላቸው፤ የገለልተኛ አስማሚ ስርዓት ገለልተኛ ሆኖ የሚቋቋም በመሆኑ ግብር ከፋዩ የሚገጥመውን ችግር መፍቻ ተጨማሪ አማራጭ ነው ብለዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጀ፤ የማሻሻያ ረቂቅ አዋጁ ኢኮኖሚው በሚያመነጨው ልክ ገቢን ለመሰብሰብና የታክስ አስተዳደርን ለማዘመን እንደሚያስችል ተናግረዋል። በአስረጂ መድረኩ ግልፅ ያልሆኑ ጉዳዮች ይበልጥ ማጥራት የሚያስችል ማብራሪያ መሰጠቱን ጠቁመው የተደረጉት ማሻሻያዎች ፍትሐዊነትንና የሕግ ተገዢነትን የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል።