ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
እንቁላል ሳይበላሽ ለሁለት ዓመት እንዲቆይ የሚያስችል ቴክኖሎጂ ለሕብረተሰቡ እየተዋወቀ ነው
Apr 30, 2026 22
ጎንደር፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡- የጎንደር ዩኒቨርሲቲ የዶሮ እንቁላል ሳይበላሽ ለሁለት ዓመት ያህል ማቆየት የሚያስችል ቴክኖሎጂን ወደ ተግባር ለማስገባት ለዶሮ ዕርባታ፣ ለአርሶ አደሮችና ለግለሰቦች ተግባር ተኮር ሥልጠና እየሰጠ ነው።   በዩኒቨርሲቲው የእንስሳት ሕክምናና ሳይንስ ኮሌጅ መምህርና ተመራማሪ ዶክተር ማስተዋል ብርሃን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ዩኒቨርሲቲው የእንቁላል ምርት ብክነትና ብልሽትን ለማስቀረት ሲሠራ ቆይቷል።   በዚህም እንቁላልን እስከ ሁለት ዓመት ሳይበላሽ ማቆየት የሚያስችል ቴክኖሎጂን የማላመድና የማስተዋወቅ ሥራ እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል። ቴክኖሎጂው በአንድ ሊትር ውኃ ውስጥ 30 ግራም የኖራ አፈር ወይም ላይም ስቶን ጨምሮ በማዋሃድ እስከ 12 እንቁላሎችን ሳይበላሽ የሚያስቀምጥ በመሆኑ ለአርሶ አደሩ ተመራጭ ነው ብለዋል። በተለይም በጾም ወራት የእንቁላል ምርት ይዘቱን በጠበቀ መልኩ በማቆየት በፍስክ ወቅት ለመጠቀም የሚያስችል መሆኑ ለሀገራችን ተመራጭ ነው ሲሉ ገልጸዋል። የኖራ አፈር ወይም ላይም ስቶን እንቁላል ቶሎ እንዳይበላሽ የሚያግዝ ካልሽየም ካርቦኔት የተባለ ውህድ እንዳለው አስገንዝበዋል።   የዶሮ እንቁላሎቹ ወደ ተዘጋጀው ማቆያ ከመግባታቸው በፊት በቅድሚያ ንጹህና ምንም አይነት ቆሻሻና ርጥበት በላያቸው ላይ አለመኖሩን ማረጋገጥ እንደሚገባም አስረድተዋል። እንደ አካባቢው የአየር ሁኔታ አንድ እንቁላል ሳይበላሽ መቆየት የሚችለው እስከ ሁለት ሳምንት መሆኑን ጠቁመው፤ ቴክኖሎጂው ይህን ችግር በመሰረታዊነት የሚቀይር መሆኑን ተናግረዋል። ቴክኖሎጂውን በስፋት በማስተዋወቅና በማላመድ ረገድም ተግባር ተኮር ሥልጠናዎችን በመስጠት ችግር ፈቺነቱን የማሳየት ሥራ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል።   ቴክኖሎጂው የሀገሪቱን የእንቁላል ብክነት በከፍተኛ ደረጃ በመቀነስ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተያዘውን ግብ ለማሳካት አስተዋጽኦ አለው ያሉት ደግሞ የዘርፉ ተመራማሪ ዶክተር አንማው እሸቴ ናቸው፡። ያደጉት ሀገራት ለበርካታ ዓመታት ሲጠቀሙበት የቆዩና ውጤታማነቱ በተግባር ተፈትሾ የተረጋገጠ ቴክኖሎጂ መሆኑን ገልጸው፤ ለሀገራችን ዶሮ አርቢዎች አዲስና አዋጭ መሆኑን ጠቁመዋል።
በፋይናንስ ዘርፍ የተደረገው ሪፎርም ውስን የሆነውን የመንግሥት ሀብት ከብክነት ታድጓል
Apr 30, 2026 50
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በፋይናንስ ዘርፍ የተደረገው ሪፎርም ውስን የሆነውን የመንግሥት ሀብት ከብክነት ለመታደግ ማስቻሉን የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ገለጸ። ቢሮው "ውጤታማ የፋይናንስ አሥተዳደር ለክልላችን ሁለንተናዊ ብልጽግና" በሚል መሪ ሐሳብ የ2018 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ በወላይታ ሶዶ ከተማ እያካሄደ ነው። በምክትል ርዕሠ መሥተዳድር ማዕረግ የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ተፈሪ አባተ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ በክልሉ በፋይናንስ ዘርፍ የተደረገው ሪፎርም ውስን የሆነውን የመንግሥት ሀብት ከብክነት ለመታደግ አስችሏል። በዚህም ያለፉትን ዘጠኝ ወራት ጨምሮ በ2 ዓመት ተኩል ውስጥ በተለያዩ ዘርፎች 50 ቢሊየን ብር ካፒታል ያስመዘገቡ 536 ፕሮጀክቶች ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። ይህም በክልሉ ውጤታማ የፋይናንስ አሥተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት በተከናወኑ ሥራዎች የመጣ ውጤት መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ መንግሥት በ2018 በጀት ዓመት ከ62 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር በላይ ካፒታል በምክር ቤት አጸድቆ በመደበኛና በካፒታል ለይቶ በመደልደል ወደ ሥራ የገባ ሲሆን፤ በዚህም ተስፋ ስጪ ለውጦች እየተመዘገቡ ነው ብለዋል። የመንግሥትን በጀት በአግባቡ ሥራ ላይ በማዋል የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሁሉም የዘርፉ አመራሮች እና የሴክተር መሥሪያ ቤቶች የፋይናንስ አሠራር ሥርዓቱን መቆጣጠር እንዳለባቸውም አሳስበዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሀገር ግንባታ እና የአፍሪካ አቪየሽን ልህቀት ተምሳሌት ነው- የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች
Apr 30, 2026 32
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሀገር ግንባታ ጉልህ ሚናው ብሔራዊ ኩራትን ከመፍጠር ባለፈ የአፍሪካ አቪየሽን የልህቀት ተምሳሌት መሆኑን የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተመሰረተበትን 80ኛ ዓመት በማስመልከት ከደንበኞችና አጋሮች ጋር የደንበኞች ተሞክሮ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።   በመድረኩ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ፣ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ(ዶ/ር)፣ የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በመድረኩ የአየር መንገዱን አገልግሎት በተመለከተ በከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች የፓናል ውይይት ተካሂዷል። የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ እንዳሉት፥ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የላቀ ውጤት ያለውና ለረጅም ዓመታት ስኬትን ማስቀጠል ያስቻለ ግዙፍ የመንግሥት የንግድ ኩባንያ ነው።   አየር መንገዱ ለኢትዮጵያ ሀገረ መንግስት ግንባታና በፖለቲካ፣ ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም ማህበራዊ ዕድገት አስተዋጽኦ ያለው ተቋም ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ከሌሎች ሀገራት ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እንዲሁም የሀገር ውስጥ ትስስርን ለማጠናከር ትልቅ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑንም አንስተዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፥ አየር መንገዱ የሀገር ኩራት የሆነ ሁሉም የኔ የሚለው የጋራ ማንነት መገለጫ ብሔራዊ ድርጅት መሆኑን ገልጸዋል።   አየር መንገዱ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ በዘርፉ የመቻልና የልህቀት ማሳያ የሆነ ተቋም መሆኑን አንስተው፥ የኢትዮጵያን የማድረግ አቅም ማሳያ እንደሆነም ተናግረዋል። አየር መንገዱ ለአገልግሎት ዘርፍ ኤክስፖርት ከፍተኛ ድርሻ እንዳለው ጠቅሰው፥ ለንግድ መሳለጥና ለሥራ እድል ፈጠራ ከፍተኛ ሚና እየተወጣ እንደሚገኝ አንስተዋል። የብሔራዊ ባንክ ገዥ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) አየር መንገዱ ግዙፍ የሎጅስቲክስ መሠረተ ልማት አቅም መገንባቱን ገልጸው፥ ለወጪ ንግድ እንዲሁም ለዲፕሎማሲ ትልቅ ሚና ያለው ተቋም ነው ብለዋል። አየር መንገዱ ነገን ዛሬ እየገነባ የሚገኝ አኩሪ ኩባንያ መሆኑንም ተናግረዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #የኢትዮጵያ_አየር_መንገድ
ባሕር ዳር ከተማን ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Apr 30, 2026 25
ባሕር ዳር፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡- የባሕር ዳር ከተማን የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት የስበት ማዕከል ለማድረግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን የከተማ አሥተዳደሩ ምክትል ከንቲባ አስሜ ብርሌ ገለጹ። የከተማ አሥተዳደሩ የዘጠኝ ወራት የመንግሥትና የፓርቲ የሥራ አፈፃፀም የግምገማ መድረክ በባሕር ዳር መካሔድ ተጀምሯል።   ምክትል ከንቲባው በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የሕዝቡን የልማት ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ እና የከተማዋን ገፅታ በተሻለ ደረጃ መቀየር የሚያስችሉ የልማት ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ነው። ባለፉት ዘጠኝ ወራትም የከተማዋን ሰላም አስተማማኝ ከማድረግ ባለፈ፤ ማራኪ፣ ለነዋሪዎች ብሎም ለጎብኝዎችና ለኢንቨስትመንት የተመቸች በማድረግ በኩል የተሻለ ውጤት መመዝገቡን ጠቅሰዋል። ሕዝቡንና ባለሃብቱን በማሳተፍ የመዝናኛ ቦታዎችን በመገንባት፤ የአረንጓዴ እና የፓርክ ልማት ሥራዎች ተጨማሪ ገቢና የሥራ ዕድል እንዲፈጥሩ መደረጉን ጠቁመዋል። መሶብ የአንድ ማዕከልን ወደ ሥራ በማስገባት 72 አገልግሎቶችን በተቀላጠፈ አግባብ ለተጠቃሚዎች ተደራሽ ማድረግ መቻሉንም አስታውቀዋል። በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በገቢ አሰባሰብ፣ ኢንቨስትመንትን በመሳብና፣ የዜጎችን የመኖሪያ ቤት አቅርቦት ችግር ለመፍታት ጠንካራ ሥራዎችን ማከናወን እንደተቻለም አስረድተዋል።   የባሕር ዳር ከተማ አሥተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሞላ ሁሴን በበኩላቸው፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የከተማውን ሕዝብና ወጣት በማሳተፍ በተሠራው የሰላም ማስከበር ሥራ አስተማማኝ ሰላም ማስፈን እንደተቻለ ገልፀዋል። ይህን ተከትሎም የልማት ሥራዎችን ያለምንም ስጋት ማከናወን የሚያስችል ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ስኬታማ በሆነ አግባብ እንዲካሄድ ተፎካካሪ ፓርቲዎችን ያካተተ ምክር ቤት ተቋቁሞ ውጤታማ ተግባራትን ማከናወን እንደተቻለም አንስተዋል። በቀጣይም የምርጫ ሥራዎችን ጨምሮ የልማትና የመልካም አሥተዳደር ሥራዎች ሕዝብን ባሳተፈ አግባብ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አመላክተዋል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በ80 ዓመታት ጉዞ ፈተናን ወደ ዕድል በመቀየር አህጉራዊ ምልክትነቱን እያስቀጠለ ነው
Apr 30, 2026 86
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2018(ኢዜአ) ፦የኢትዮጵያ አየር መንገድ በ80 ዓመታት ጉዞ ፈተናን ወደ ዕድል በመቀየር አህጉራዊ ምልክትነቱን እያስቀጠለ እንደሚገኝ የአየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ የተመሰረተበትን 80ኛ ዓመት በማስመልከት ከደንበኞችና አጋሮች ጋር የደንበኞች ተሞክሮ መድረክ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ የገንዘብ ሚኒስትር አሕመድ ሽዴ፣ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር)፣ የብሔራዊ ባንክ ገዢ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) እንዲሁም ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል። በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው እንዳሉት፤ አየር መንገዱ ባለፉት ስምንት አስርት ዓመታት የዕድገትና ስኬት ጉዞዎችን በማድረግ ዛሬ ያለበት ደረጃ ደርሷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በካይሮ አንድ ብሎ በረራ የጀመረውን የዓለም አቀፍ የበረራ አገልግሎት አሁን ላይ መዳረሻውን ወደ 145 ማስፋቱን ተናግረዋል። በዚህም 147 ዘመናዊ አውሮፕላኖች ባለቤት በመሆን በዓመት ከ20 ሚሊየን በላይ መንገደኞች ማስተናገድ የሚያስችል አስተማማኝ አቅም መገንባቱንም ገልጸዋል። አየር መንገዱ ለደንበኞች ምስጉን አገልግሎት በመስጠት ዓለም አቀፍ ዕውቅናና ሽልማት ማግኘት መቻሉንና ለመላው አፍሪካ ሞዴል የሆነ ግዙፍ አየር ማረፊያ እየገነባ መሆኑንም አብራርተዋል። ባለፉት 80 ዓመታት በርካታ ፈታኝ ወቅቶችን በስኬት በማለፍ ኢትዮጵያ የቱሪስት መዳረሻና የዓለም አቀፍ ተቋማት መናኸሪያ እንድትሆን በማስቻል አህጉራዊ ምልክትነቱን እየስቀጠለ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ስምንት ዓመታትም 74 አዳዲስ አውሮፕላኖችን ማምጣቱንና 117 አውሮፕላኖችን ማዘዙንም አብራርተዋል። በዚህም የመንገደኞችን ቁጥር በእጥፍ በማሳደግ ዓመታዊ ገቢውን 120 በመቶ እንዲሁም ትርፉንም በሦስት እጥፍ ማሳደጉን አንስተዋል። Ethiopian News Agency #ኢዜአ #የኢትዮጵያ_አየር_መንገድ
በምዕራብ ጉጂ ዞን ከ396 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር ተሸፍኗል
Apr 30, 2026 60
ቡሌ ሆራ፤ ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡- በተያዘው የበልግ ወቅት ከ396 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በዘር መሸፈኑን የምዕራብ ጉጂ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ፡፡ 387 ሺህ 954 ሄክታር መሬት በበልግ እርሻ ለማልማት ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን በጽሕፈት ቤቱ የሰብል ልማትና ጥበቃ ቡድን መሪ ታሪኩ ብዙአየሁ ለኢዜአ ተናግረዋል።   በአሁኑ ወቅትም በልግ አብቃይ በሆኑ ወረዳዎች 396 ሺህ 594 ሄክታር በተለያዩ ሰብሎች በማልማት፤ ከዕቅድ በላይ ስኬታማ ሥራዎች ማከናወን መቻሉን ገልጸዋል። በበልግ ከለማውም ከ9 ሚሊየን 100 ሺህ ኩንታል በላይ አጠቃላይ ምርት ለመሰብሰብ ታቅዷል ብለዋል። 122 ሺህ 981 ኩንታል ማዳበሪያና 133 ሺህ 240 ኩንታል ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ መዋሉንም አረጋግጠዋል። በዞኑ የሚመረቱ ዋና ዋና የሰብል ዓይነቶችም፤ ስንዴ፣ ጤፍ፣ በቆሎ፣ ቦሎቄና ሌሎች መሆናቸውን ጠቁመዋል። በትራክተር የማረስ፣ የመስመርና የኩታ ገጠም የተሻሻሉ የግብርና አሠራሮች መተግበራቸውንም ጠቅሰዋል፡፡ በበልግ አዝመራ የሰብል ልማት 294 ሺህ 360 አርሶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮች መሳተፋቸውን ገልጸዋል፡፡
ሀገራዊ ለውጡ የክልሉን ግብርና በማዘመን ወደ ላቀ የምርታማነት ምዕራፍ አሸጋግሯል-ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን
Apr 30, 2026 122
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡-ከሀገራዊ ለውጡ ወዲህ ግብርናው በቴክኖሎጂ የሚደገፍበት አሰራር መዘርጋቱ የክልሉን ምርትና ምርታማነት ወደ አዲስ ምዕራፍ ማሸጋገሩን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ገለፁ።   ከለውጡ በፊት በክልሉ ዓመታዊ የምርት መጠን 18 ሚሊዮን ኩንታል የነበረ ሲሆን፥ አሁን ወደ 60 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ማደጉን አብራርተዋል። መንግሥት ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት ልዩ ትኩረት ከሰጣቸው ብዝኃ የኢኮኖሚ ዘርፎች መካከል ግብርና አንዱ ነው። ባለፉት የለውጥ ዓመታትም የባለ አነስተኛ ይዞታ አርሶ አደሮችን የኩታ ገጠም እርሻ፣ የሜካናይዜሽን እና የግብርና ኢንቨስትመንት ላይ ትኩረት በመስጠት በዘርፉ ከፍተኛ እመርታ መጥቷል። የቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልልም ኢትዮጵያ ያስቀመጠችውን ራስን በምግብ የመቻል ግብ እንዲሳካ፣ በክልሉ የሚገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች የግብርና ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ የሚያገኙበትን ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር ትኩረት አድርጎ እየሰራ ይገኛል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን በክልሉ ከራስ ፍጆታ ባለፈ በስፋት ለገበያ በማቅረብ ረገድ ትልቅ አቅም ወደሚፈጥር የምርታማነት ምዕራፍ ሽግግር እየተደረገ ነው ብለዋል። ከለውጡ በፊት በክልሉ ዓመታዊ የምርት መጠን 18 ሚሊዮን ኩንታል የነበረ ሲሆን፥ አሁን ወደ 60 ሚሊዮን ኩንታል ማደጉን አብራርተዋል። እነዚህ ውጤቶች ሊመዘገቡ የቻሉት በክልሉ የሚከናወኑ የግብርና ልማት ሥራዎች በልዩ ልዩ ቴክኖሎጂዎች እንዲደገፉ ትኩረት አድርጎ በመሠራቱ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም በክልሉ የግብርና ልማት እንቅስቃሴዎች ላይ ባለሀብቶች እንዲሠማሩ ከማድረግ ባለፈ አርሶ አደሮች በዘርፉ በዘመናዊ መልኩ ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩም ለተመዘገበው ውጤት መነሻ ነው ብለዋል። ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ አያይዘውም የተቀናጀ የግብርና ልማት የተለያዩ የግብርና ምርት አይነቶችን በአንድ አካባቢ ማምረት የሚቻልበትን አቅም የሚያጎለብት በመሆኑ የኸልዋ አግሮ ኢንዱስትሪን በማቋቋም ወደ ስራ ተገብቷል ብለዋል። በኢንዱስትሪው እየተመረቱ ካሉ ምርቶች መካከል አትክልትና ፍራፍሬ እና የተለያዩ የእንስሳት ተዋጽኦዎች እንደሚገኙበት ተናግረዋል። በኢንዱስትሪው በተቀናጀ የግብርና ስራ ያሉ መልካም ተሞክሮዎችን ባለሀብቶች፣ ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ልምድና ተሞክሮ ቀስመው የተሻለ ስራ መስራት የሚችሉበትን ሁኔታ ለመፍጠር እየተሠራ መሆኑን ገልፀዋል።   ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሆሞሻ ወረዳ የተቀናጀ የእርሻ ልማት ስራ ላይ የተሰማሩት ፍቃዱ ነመራ በበኩላቸው፥ በ2016 ዓ.ም በመስኩ ላይ እንደተሰማሩ ያወሳሉ። በክልሉ ለግብርና ስራ ምቹ የሆነ የተፈጥሮ ጸጋ እያለ የግብርና ምርቶችን ከመሸመት ይልቅ ለምን ማምረት አልጀምርም በሚል ቁጭት ወደ ግብርና ልማት እንደገቡ ገልጸዋል። በተቀናጀ የግብርና ስራ የተለያዩ ቋሚ ተክሎችና የእንስሳት ተዋጽኦ ምርቶችን በስፋት በማምረት ከራስ ፍጆታ ባለፈ ለገበያ በማቅረብ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። በማምረት ላይ ከሚገኙት ቋሚ ተክሎች መካከል አቮካዶ፣ ፓፓያ፣ ሙዝ፣ ብርቱካንና ሌሎችም የሚገኙበት ሲሆን የማር፣ የዶሮና የእንሥሣት ምርት ላይም ትኩረት መስጠታቸውን አብራርተዋል። የሚመረቱ ምርቶችን ምርታማነት ለማሳደግ የከርሠ ምድር ውሃን በመጠቀም መስኖና የተፈጥሮ ማዳበሪያን እየተጠቀሙ ምሆኑን ገልፀዋል። በመንግሥት በኩል የሚደረጉ ክትትልና ድጋፎች በተሰማሩበት የሥራ መስክ ውጤታማ እንዲሆኑ አቅም እየፈጠረላቸው እንደሚገኝም አንስተዋል። ሁሉም ህብረተሰብ በየአካባቢው ያለውን እምቅ ጸጋ በትጋት ካለማ ኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነቷን ለማረጋገጥ የያዘችውን እቅድ እንደምታሳካ ጠቅሰው፥ ለዚህም የበኩላቸውን አሻራ በማሳረፍ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ንግድና ኢንቨስትመንትን የሚያበረታታ አስቻይ ምኅዳር ፈጥሯል-አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ
Apr 30, 2026 138
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 22/2018 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ንግድና ኢንቨስትመንትን የሚያበረታታ አስቻይ ምኅዳር መፍጠሩን በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ንግድና ኢንቨስትመንትን በማበረታታት ለዓለም አቀፍ አልሚ ባለሃብቶች ምች ምኅዳርን ፈጥሯል። የዓለም አቀፍ አልሚ ባለሃብቶችም የኢትዮጵያን ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢ በመጠቀም በተለያዩ የልማት መስኮች እንዲሰማሩ እያደረገ ይገኛል። ‎የኢንቨስትመንት ኮሚሽን የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት የዕቅድ አፈፃጸም ሪፖርት እንደሚያሳየው ኢትዮጵያ 3 ነጥብ 52 ቢሊዮን ዶላር የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ ችላለች። በኢትዮጵያ የፈረንሳይ አምባሳደር አሌክሲስ ላሜክ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ዕድገትና ብልፅግናን የሚያፋጥን ሰፊ የንግድና ኢንቨስትመንት ዕድል ያላት ሀገር ናት። የኢትዮጵያን የንግድና ኢንቨስትመንትን አማራጭ ለማስፋት መንግስት የሚወስዳቸው የፖሊሲ አማራጮችም የሚደነቁ መሆናቸውን ገልጸዋል። በኢኮኖሚ ዘርፍ ልማትን ለማበረታታት የተወሰዱ የፖሊሲ ማሻሻያ ተግባራትም ኢትዮጵያን አፍሪካዊት ተመራጭ የንግድና ኢንቨስትመንት መዳረሻ ሀገር እያደረጋት መሆኑን ተናግረዋል። በኢትጵያና ፈረንሳይ መካከል ያለውን የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነት የበለጠ ለማስፋትም በትኩረት እየሰሩ እንደሚገኝ አንስተዋል። ፈረንሳይም የሀገራቱን ትብብር የበለጠ ማጠናከር የኢትዮጵያን የንግድና ኢንቨስትመንት ዕድሎችን በመደገፍ ወደ ተሻለ የዕድገት ምዕራፍ ለማሸጋገር ድጋፍ እያደረገች መሆኗን ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅት የፈረንሳይ አልሚ ባለሃብቶች በተለያዩ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት አማራጮቻቸውን እያስፋፉ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያን ሰፊ የንግድና ኢንቨስትመንት አማራጮቻቸውን የበለጠ እንዲያሰፉ ለማስቻል በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዚህም የሁለቱን ሀገራት ሁለንተናዊ ትብብር የበለጠ በማጎልበት የጋራ ተጠቃሚነትን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
በኦሮሚያ ክልል ባለፉት 9 ወራት ከ2 ሚሊየን ለሚልቁ ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሯል
Apr 30, 2026 132
አዲስ አበባ፤ 22/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ2 ሚሊየን ለሚልቁ ዜጎች በሀገር ውስጥና በውጭ የሥራ ዕድል መፈጠሩን የኦሮሚያ ክልል የሥራ ዕድል ፈጠራና ክኅሎት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ዋሲሁን ጎልጋ ገለጹ።   ለ4 ነጥብ 5 ሚሊየን ዜጎች የሥራ ፈጠራ ሥልጠና መሰጠቱንም ገልጸዋል። ከእነዚህ መካከልም ፍላጎት ያላቸውን 2 ነጥብ 6 ሚሊየን ወጣቶች በመለየት በሥራ ዓለም ተወዳዳሪ እንዲሆኑ በቴክኒክና ሙያ ኮሌጆች በኩል የክኅሎት ማሳደጊያ ሥልጠና እንዲያገኙ መደረጉን ለኢዜአ ተናግረዋል። ከዞን እስከ ቀበሌ ድረስ ያሉትን ተጨባጭ ሁኔታዎች መሠረት በማድረግ፤ በኢንዱስትሪ፣ በግብርና እና በአገልግሎት ዘርፎች የተለዩ የሥራ ዕድሎች መፈጠራቸውንም አስረድተዋል።   ይህ የሥራ ዕድል ፈጠራ ሂደትም በክኅሎት ላይ የተመሠረተ እንዲሆን በማድረግ ዜጎች በየመስካቸው ውጤታማ እንዲሆኑ መሠራቱን አረጋግጠዋል። በበጀት ዓመቱ 2 ሚሊየን 720 ሺህ ዜጎችን በማደራጀትና በቅጥር የሥራ ዕድል ለመፍጠር መታቀዱን ጠቁመው፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሀገር ውስጥ ለ2 ሚሊየን 17 ሺህ 208 ዜጎች እንዲሁም 159 ሺህ ዜጎች በውጭ ሀገራት የሥራ ስምሪት እንዲያገኙ ተደርጓል ብለዋል።   ለሥራ ዕድል ተጠቃሚዎቹ ምቹ ሁኔታን ከመፍጠር አንጻርም፤ 95 ሺህ ሄክታር መሬት ለማምረቻ፣ ከ7 ሺህ በላይ የመሸጫ ሼዶች እንዲሁም ከ23 ቢሊየን ብር በላይ የፋይናንስ አቅርቦት መመቻቸቱን ተናግረዋል። ወደ ሥራ የገቡ ዜጎች ለሚያመርቷቸው ምርቶች ሰፊ የገበያ ትስስር እንዲፈጠር መደረጉን ገልጸው፤ በዚህም ውጤታማ የሆኑ 1 ሺህ 800 ኢንተርፕራይዞች ወደ ኢንቨስትመንት ደረጃ እንዲሸጋገሩ መደረጉን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የቻይና ባለሃብቶችን የንግድና ኢንቨስትመንት ተሳትፎ እያሳደገ ነው
Apr 29, 2026 696
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የቻይና ባለሃብቶችን የንግድና ኢንቨስትመንት ተሳትፎ እያሳደገ መሆኑን በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ቼን ሃይ ገለጹ። አምባሳደር ቼን ሃይ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ እና ቻይና ታሪካዊና ጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነት ያላቸው ሀገራት ናቸው። የኢትዮ-ቻይና ታሪካዊ ግንኙነት የልማት ትብብርን በማጎልበት የሀገራቱን ሁለንተናዊ ግንኙነት እያጠናከረ እንደሚገኝም ገልጸዋል። የሀገራቱ የሁለትዮሽ የንግድና ኢንቨስትመንት ስትራቴጂክ አጋርነት ከፍተኛ ዕድገት በማስመዝገብ የጋራ ተጠቃሚነትን እያረጋገጠ መሆኑን ተናግረዋል። የቻይና ባለሃብቶች በኢትዮጵያ የሚሰማሩባቸው አዳዲስ የንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፎችም ከፍተኛ ዕድገት እያስመዘገቡ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያም የቻይና አልሚ ባለሃብቶችን የኢንቨስትመንት በራስ መተማመን በማጎልበት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አስረድተዋል። ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያው የፈጠረው የኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢም አዳዲስ ዕድሎችን መጠቀም የሚሹ በርካታ የቻይና ባለሀብቶችን እየሳበ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። የኢትዮ-ቻይና የኢኮኖሚ ትብብርም በግብርና፣ ኢንዱስትሪና የሰው ሃብት ልማት ሶስት ወሳኝ ምሰሶዎችን ማዕከል በማድረግ በስፋት እየተሰራበት መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ፈጣን የልማትና የዕድገት አቅጣጫ የሀገራቱን ስትራቴጂክ አጋርነት በማጠናከር ከፍተኛ አቅም መፍጠሩን ገልጸዋል። የቻይና ባለሃብቶች የኢትዮጵያ የንግድና የአምራች ኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት ተሳትፎም የኢኮኖሚ ልማትና ሽግግርን በማፋጠን ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ተናግረዋል። የሀገራቱ በሰው ሃብት ልማት ትብብር የአዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ዘርፍ በክህሎት የበለፀጉ ዜጎችን በማፍራት ወሳኝ ሚና እየተወጣ መሆኑን አስገንዝበዋል። በሚቀጥሉት ዓመታትም የሀገራቱን የንግድና ኢንቨስትመንት ስትራቴጂክ አጋርነት የበለጠ በማጠናከር የሁለትዮሽ ግንኙነትን የበለጠ ለማጠናከር እንደሚሰራ ጠቅሰዋል።
በክልሉ ኢንተርፕራይዞችን ወደ ኢንዱስትሪ ለማሸጋገር የተከናወኑ ተግባራት ውጤት አስገኝተዋል
Apr 29, 2026 435
ሆሳዕና፤ ሚያዝያ 21/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ኢንተርፕራይዞችን በመደገፍና በማብቃት ወደ ኢንዱስትሪ ለማሸጋገር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤት ማስገኘታቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ፡፡ የክልሉ ስራ እድል ፈጠራ ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ "የኢንተርፕራይዞች ሽግግር ለእመርታዊ እድገት" በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጀው አውደ ርዕይና ባዛር እንዲሁም የሞዴል ኢንተርፕራይዞች ደረጃ ሽግግር እውቅና መርሃ ግብር በሆሳዕና ከተማ ተካሂዷል፡፡   ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት በክልሉ ኢንተርፕራይዞችን በማብቃት ወደ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ለማሸጋገር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተስፋ ሰጪ ውጤት አስገኝተዋል። ኢንተርፕራይዞቹ ከውጪ የሚገቡ ምርቶችን በሀገር ውስጥ በመተካትና ለውጪ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ከማምረት በተጨማሪ ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል እየፈጠሩ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል።   በክልሉ ተወዳዳሪ ኢንተርፕራይዞችን ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የክልሉ ስራ እድል ፈጠራ ኢንተርፕራይዝ ልማት ቢሮ ኃላፊ ሙስጠፋ ኢሳ ናቸው።   በገጠርና በከተማ በአነስተኛና መካከለኛ አምራች ዘርፍ ከ25 ሺህ በላይ ኢንተርፕራይዞች በተለያዩ መስኮች መሰማራታቸውን ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በክልሉ በጥቃቅንና አነስተኛ ደረጃ የሚገኙ 4ሺህ 948 ኢንተርፕራይዞችን የማሸጋገርና 495 ሞዴል ኢንተርፕራይዞችን የመለየት ስራ መሰራቱን ገልጸዋል። አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል በሆሳዕና ከተማ የሚገኘው የጡማ ፕላስቲክ ፋብሪካ ዋና ስራ አስኪያጅ ሰለሞን ታሪኩ እና የእንጨትና የብረታብረት ማምረቻ ኢንተርፕራይዝ ሰብሳቢ ወጣት ዘርፍነሽ ሽብሩ የደረጃ ሽግግሩ ድርጅቶቻቸው ስራቸውን በተጠናከረ ሁኔታ እንዲከውኑ ማስቻሉን ጠቁመዋል። ፋብሪካው ከ120 ሚሊየን ብር በላይ ካፒታል ማስመዝገቡንና ከ150 በላይ ለሚሆኑ ዜጎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል መፍጠሩን አቶ ሰለሞን ተናግረዋል። ወጣት ዘርፍነሽ በበኩሏ ኢንተርፕራይዙ 10 ሚሊየን ብር ካፒታል ማስመዝገቡን ገልጻ 30 ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል ፈጥሯል ብላለች።
ኢትዮጵያ የአቪዬሽን መሰረተ ልማት በማሟላት የአፍሪካ አቪዬሽን መግቢያ በር መሆን የሚያስችላት ቁመና ላይ ናት
Apr 29, 2026 385
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአቪዬሽን መሰረተ ልማት በማሟላት የአፍሪካ አቪዬሽን መግቢያ በር መሆን የሚያስችላት ቁመና ላይ ናት ሲሉ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በረኦ ሀሰን ገለጹ። ዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማህበር ከኢትዮጵያ አየር መንገድ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ጉባኤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል። ለሁለት ቀናት በሚቆየው በዚህ ጉባኤ በአፍሪካ አቪዬሽን ዘርፍ ባሉ ችግሮች እና መፍትሔዎች ላይ ምክክር ይደረጋል። የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በረኦ ሀሰን እንደገለጹት፤ አፍሪካ አንድ ነጥብ አራት ቢሊየን የህዝብ ቁጥር ያላት ቢሆንም አህጉሪቱ በበቂ መጠን በአየር ትራንስፖርት ተሳስራለች ማለት አይቻልም።   ለዚህም የዋጋ መጨመር፣ የመሰረተ ልማት በበቂ ደረጃ አለመሟላት እና ወጥ የሆነ የአሰራር ስርዓት አለመኖር ዋነኞቹ ምክንያቶች መሆናቸውን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ እንደ ሀገር በአቪዬሽን መሰረተ ልማት ላይ በሰፊው ኢንቨስት በማድረግ ላይ መሆኗን በመጠቆም፤ በቢሾፍቱ ግንባታው የተጀመረው ዓለምአቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክትም ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸዋል። ግንባታው ሲጠናቀቅም የኢትዮጵያን አቅም ከማሳደጉ ባሻገር አፍሪካን ከተቀረው ዓለም ጋር ለማስተሳሰር ጉልህ ሚና እንደሚጫወት አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ዘርፍ መሰረተ ልማት ላይ የምታከናውነው ሥራ ሀገሪቷን የአፍሪካ አቪዬሽን መግቢያ በር (ጌት ዌይ) የሚያደርጋት መሆኑንም ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን በጠንካራ ሪፎርም ውስጥ እንዲያልፍ መደረጉን ጠቁመው፤ ይህም በኢትዮጵያ ምቹና ደህንነቱ የተጠበቀ የበረራ አገልግሎት እንዲኖር በማድረግ ጠንካራ ተቆጣጣሪ ተቋም እንዲፈጠር ማስቻሉን አብራርተዋል። በአፍሪካ አቪዬሽን ዘርፍ ለሚስተዋሉ ችግሮች ዘላቂ እልባት ለማበጀት በጋራ መስራት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ችግሮችን ከመለየት ባለፈ ተግባራዊ የመፍትሔ እርምጃዎችን መውሰድ እንደሚገባ አሳስበዋል። ኢትዮጵያም በመስኩ ያሉ ማነቆዎች እንዲፈቱ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በጋራ ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗንም አረጋግጠዋል።   የዓለም አቀፍ ሲቪል አቪየሽን ድርጅት የምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር ሉሲ ቡግዋ በበኩላቸው፤ የአፍሪካን የአቪየሽን ትስስር ለማፋጠን ሀገራት በትብብር ሊሰሩ ይገባል ብለዋል። በአፍሪካ ደኅንነቱ የተጠበቀ የአቪየሽን መሠረተ ልማት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።   የአፍሪካ አየር መንገዶች ማኅበር ዋና ጸኃፊ አብድራህማን በርቴ፤ የአህጉሪቱን የበራራ ግንኙነት ለማፋጠን በርካታ ሀገራት የአፍሪካ የተቀናጀ የአየር ትራንስፖርት ገበያ የትብብር ማዕቀፍ መፈረማቸውን ገልጸዋል። ሀገራቱም የትብብር ስምምነት ማዕቀፉን ከመፈረም ባሻገር ወደ ተግባር እንዲለወጥ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል ብለዋል።   የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው በበኩላቸው፤ አየር መንገዱ አህጉሪቱን በአቪየሽን ልማት በማስተሳሰር የሚጠበቅበትን ገንቢ ሚና እየተወጣ ነው ብለዋል። በቀጣይም ከአፍሪካ የአቪየሽን ኢንዱስትሪ ተዋናዮች ጋር በመተባበር አህጉሪቱን ለማስተሳሰር በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
በጋምቤላ ክልል ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ3 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ ተሰበሰበ
Apr 29, 2026 130
ጋምቤላ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከተለያየ የገቢ አርዕስት ከ3 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ ቸንኮት ዴቪድ ገለጹ። በተያዘው የበጀት ዓመት ከተለያየ የገቢ አርዕስት ከ7 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ ለመሰብሰብ ግብ ተጥሎ እየተሠራ መሆኑን ኃላፊው ለኢዜአ ተናግረዋል። በዚህም መሠረት ባለፉት ዘጠኝ ወራት በክልሉ የነበሩ ፈተናዎችን በመቋቋም ከቀጥታ ታክስ፣ ቀጥታ ካልሆኑና ከሌሎች የገቢ አርዕስት ከ 3 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉን አረጋግጠዋል። ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከ1 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር በላይ ብልጫ አለው ብለዋል። የተጀመሩ የገቢ አሰባሰብ ተግባራትን በማጠናከር ዓመታዊ ዕቅዱን ለማሳካት ርብርብ እንደሚደረግ ጠቁመዋል። ግብር መክፈል ሕዝቡ የሚፈለገውን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሠረተ-ልማቶችን ለማሟላት ያለው ፋይዳ የጎላ በመሆኑ፤ ዜጎች የሚጠበቅባቸውን ግብር በመክፈል ሀገራዊ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል።
በጎንደር ከተማ ገጠር ቀበሌዎች ለ100 ሺህ የእርሻ መሬት ባለይዞታዎች ዲጂታል ካርታ እና የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር ሊሰጥ ነው
Apr 29, 2026 115
ጎንደር፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በጎንደር ከተማ አስተዳደር በገጠር ቀበሌዎች ለ100 ሺህ የእርሻ መሬት ባለይዞታዎች ዲጂታል ካርታ እና የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር ለመስጠት እየተሰራ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ መሬት መምሪያ አስታወቀ፡፡ በከተማው ገጠር ቀበሌዎች ለመሬት ባለይዞታዎች የማረጋገጫ ደብተር ለመስጠት የካዳስተር ሥራ ማስጀመር የሚያስችል የአጋር አካላት የምክክር መድረክ ዛሬ ተካሂዷል፡፡   የመምሪያው ምክትል ሃላፊ አዛናው መልካሙ በመድረኩ እንደገለጹት፤ ዘመናዊ የዲጂታል የመሬት ምዝገባ ስርአት የአርሶ አደሩን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ በዘላቂነት የሚፈታ ነው፡፡ በከተማው በታቀፉ 11 የገጠር ቀበሌዎች ለ100 ሺህ የእርሻ መሬት ባለይዞታዎች 2ኛ ደረጃ ዲጂታል ካርታና የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር ለመስጠት እየተሰራ ነው ብለዋል። በዚህም 1ሺህ 283 ባለይዞታዎች ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ገልጸው፣ ማረጋገጫው መሰጠቱ አርሶ አደሩ ህጋዊ የመሬት ባለቤትነቱን በማረጋገጥ መሬቱን ለመንከባከብና ለማልማት ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል ብለዋል። በተጨማሪም የማረጋገጫ ካርታውን አስይዞ ከአበዳሪ ተቋማት የገንዘብ ብድር እንዲያገኝ ዋስትና እንደሚሰጠው ገልጸው፣ በመሬት ይገባኛል የሚነሱ ግጭቶችን እንደሚያስወግድም አስረድተዋል። ዲጂታል የይዞታ ማረጋገጫ ካርታና ደብተር የመስጠት ሥራውን በተያዘው የሚያዚያ ወር መጨረሻ በማስጀመር እስከ ቀጣዩ ዓመት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስገንዝበዋል። የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ተወካይ መኮንን ተሾመ በበኩላቸው፤ መሬት ትልቅ ሀብት በመሆኑ መረጃውን በሳይንሳዊ መንገድ ሰንዶ ለሚፈለገው ልማት ማዋል ይገባል ብለዋል። በጎንደር ከተማ የአንቸው ገጠር ቀበሌ ነዋሪ ሴት አርሶ አደር ተዘሩ አለማየሁ፤ ከዚህ በፊት የተሰጣቸው የመጀመሪያ ደረጃ የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር ከባንክ ብድር አውጥተው በልማት ስራ ለመሰማራት እንቅፋት እንደሆነባቸው አስታውሰዋል።   አዲሱ ዲጂታል የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ ከባንክ ለመበደር ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ገልጸው፣ ካርታውን ለማግኘት አስፈላጊውን የባለቤትነት ማስረጃዎች አደራጅቼ እየጠበኩ ነው ብለዋል። ዲጂታል የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ካርታ የመሬት ወረራን ለማስቀረት ትልቅ ፋይዳ አለው ያሉት ደግሞ በከተማ አስተዳደሩ የሳቢያ ሳይና ገጠር ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር እያዩ አሊ ናቸው፡፡   በምክክር መድረኩ ከገጠር ቀበሌዎች የተውጣጡ አርሶ አደሮች፣ የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡
በክልሉ የበጀት አስተዳደርና አጠቃቀምን በማዘመን በህዝብ ለሚነሱ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ የመስጠቱ ተግባር ይጠናከራል
Apr 29, 2026 140
ጋምቤላ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል የበጀት አስተዳደርና አጠቃቀምን በማዘመን በህዝብ ለሚነሱ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ የመስጠቱ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተገለጸ። በፕሮግራም በጀት አሰራርና አተገባበር ዙሪያ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችና ባለሙያዎች የተሳተፉበት የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ እየተካሄደ ነው። የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ተወካይ አቶ ኡቶው ኡኮት በመድረኩ ላይ እንዳሉት ፤በክልሉ እየተመዘገበ ያለውን ኢኮኖሚያዊ እድገት ለማስቀጠል የበጀት አስተዳደርና አጠቃቀምን ማዘመን ያስፈልጋል ። ለዚህም ክልሉ ያለውን ውስን በጀት በአግባቡ በማስተዳደር በህዝብ ለሚነሱ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ተግቶ መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል። በዚህ ረገድ ክልሉ ባለፉት ዓመታት ያለውን ውስን በጀት ስራ ላይ በማዋል የህዝቡን የማህበራዊና የኢኮኖሚያዊ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። በቀጣይም የፋይናንስ አሰራርና አጠቃቀም ሂደቱን ይበልጥ በማዘመን የክልሉን ልማትና እድገት ለማፋጠን በቁርጠኝነት ሊሰራ ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። መንግስት እቅድና በጀት ከውጤት ጋር በማስተሳሰር ቀጣይነት ያለውና ተጨባጭ ውጤት ለማስመዝግብ የሚያስችል’’የፕሮግራም በጀት’’ፖሊሲ ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩንም ገልጸዋል። በመሆኑም እንደ ሀገር ለተጀመረው የፕሮግራም በጀት ማሻሻያ ፖሊሲ ትግበራ ስኬታማነት የክልሉ አመራሮችና ባለሙያዎች በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ ተወካዩ አስገንዝበዋል። የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ኡማን አሙሉ (ዶ/ር) በበኩላቸው ፤ባለፉት ዓመታት ሲተገበር የቆየው የበጀት አጠቃቀምና አሰራር በርካታ ለውጦች የታዩበት ነው ብለዋል። ቀልጠፋና ውጤታማ የበጀት አስተዳደርን ከማስፈን አንፃር ውስንነቶች እንደነበሩ አመልክተው ይሕንን ለመቀየር ይሰራል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅት በክልሉ የሚተገበረው የፕሮግራም በጀት ቀደም ሲል የነበሩ ክፍተቶችን እንደሚያስቀር ጠቁመው ለተግባራዊነቱ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ጠይቀዋል።
በከተማው በትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የተስተዋለውን ክፍተት ለማረም በተሰራው ሥራ ለውጥ መጥቷል
Apr 29, 2026 161
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በወላይታ ሶዶ ከተማ ከነዳጅ እጥረት ጋር በተያያዘ በህዝብ የትራንስፖርት አገልግሎት ላይ የነበረውን ክፍተት ለማረም በተሰራው ሥራ ለውጥ መምጣቱን ተሳፋሪዎችና አሽከርካሪዎች ገለጹ። የወላይታ ሶዶ ከተማ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መምሪያ በበኩሉ አገልግሎቱን ለማስተጓጎልና ህዝቡን ለማማረር በሚሰሩ አሽከርካሪዎች ላይ የሚደረገው ክትትልና ቁጥጥር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጿል። ከወላይታ ሶዶ ከተማ ወደ ሻሸመኔ እና ሀዋሳ ከተሞች ሲጓዙ የነበሩት ወይዘሮ ብዙአየሁ ሊዮን እና ፓስተር ዳዊት ደግሰው የነዳጅ እጥረቱን ምክንያት በማድረግ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ሲገጥም የነበረው እንግልት መፈታቱን ተናግረዋል። የትራንስፖርት አገልግሎቱን ለማስተጓጎል በሞከሩ አሽከርካሪዎች ላይ መንግስት ክትትል አድርጎ የእርምት እርምጃ መውሰድ በመጀመሩ እንግልቱ ከመቅረቱ ባለፈ በተቀመጠው የታሪፍ ክፍያ መጓዝ እንደቻሉ ገልጸዋል። አስተያየታቸውን የሰጡ አሽከርካሪዎችም በኩፖን በሚቀዱት ነዳጅ በተቀመጠው ታሪፍ መሰረት የትራንስፖርት አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በከተማው ትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ መምሪያ ነዳጅ በተራና በኩፖን የሚቀዱበት ሁኔታ መመቻቸቱ ችግሩን እያቃለለው መምጣቱን ገልጸው፣ ህገወጥ ተግባር በሚፈጽሙ አሽከርካሪዎች ላይ በተጀመረው ክትትልና ቁጥጥር ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። የወላይታ ሶዶ ከተማ ትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ መምሪያ ኃላፊ መቅደስ በዛብህ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ወቅታዊውን የነዳጅ እጥረት ምክንያት በማድረግ የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎትን ለማስተጓጎል በሞከሩ አካላት ላይ ክትትል በማድረግ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ተናግረዋል።   ከወላይታ ሶዶ መናኸሪያ በ62 የስምሪት መስመሮች የሚነሱ ከ1 ሺህ 500 በላይ ተሽከርካሪዎች ነዳጅ በኩፖን እንዲቀዱ መደረጉን ገልጸዋል። በህግ አግባብ የማይንቀሳቀሱትን ለተወሰነ ጊዜ ከስምሪት የማስወጣትና በገንዘብ የሚቀጡበት ስርዓት መዘርጋቱን ገልጸው፣ በኩፖን የቀዱትን ነዳጅ ለታለመለት ዓላማ ያላዋሉ አሽከርካሪዎች መቀጣታቸውን ተናግረዋል። በዚህም በአሁኑ ወቅት የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት ላይ ሲስተዋል የነበረው ችግር እየተፈታ መምጣቱን ገልጸው፣ ክትትሉ ይጠናከራል ብለዋል።   የወላይታ ሶዶ ከተማ ፖሊስ መምሪያ አዛዥ ኮማንደር ሀብታሙ አሰፋ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ በተለያዩ ማደያዎች ጨለማን ተገን በማድረግ በህገ ወጥ መንገድ ነዳጅ ሲሸጡ የተገኙ ከአምስት በላይ ግለሰቦች በቁጥጥር ስር ውለው ምርመራ ተጀምሯል። እንዲሁም ከህግ ውጭ ሲዘዋወር የነበረ 9ሺህ 700 ሊትር በላይ ናፍጣ እና 2 ሺህ 259 ሊትር በላይ ቤንዚን ተይዞ ለመንግስት ገቢ መደረጉን ገልጸው፣ ነዋሪው ህገወጥ ድርጊትን በመከላከል እያደረገ ያለውን ተሳትፎ አድንቀዋል።
በብሔረሰብ አስተዳደሩ በመጪው መኸር ወቅት ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
Apr 29, 2026 75
ሰቆጣ ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በ2018/19 የመኸር ወቅት ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ለመቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት ትኩረት መደረጉ ተገለጸ። መምሪያው የ2018/19 የመኸር እርሻ የንቅናቄ መድረክ በሰቆጣ ከተማ አካሄዷል። የብሔረሰብ አስተዳደሩ ምክትል አስተዳዳሪና የኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት መምሪያ ሃላፊ አቶ ሹመት ጥላሁን እንደገለጹት፤ ምርታማነትን ለማሳደግ የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችንና አሰራሮችን ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ ነው። አስተዳደሩ ዝናብ አጠር በመሆኑ አካባቢውን መሰረት ያደረገ የሰብል ልማት ለማካሄድ ከምርምር ተቋማት፣ ከአርሶ አደሩና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም የሰብል ምርታማነትን በየደረጃው በማሳደግ አርሶ አደሩን ከተረጂነት ለማላቀቅ ከላይ እስከ ታች ያለው አመራርና ባለሙያ ርብርብ ማድረግ እንዳለበትም አሳስበዋል። የብሔረሰብ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ በበኩላቸው፤ በመጪው የመኸር ወቅት 120 ሺህ 638 ሄክታር መሬትን በዘር በመሸፈን 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዷል። የታቀደውን ምርታማነት ለማሳካትም 44 ሺህ ኩንታል ሰው ሰራሽ ማዳበሪያና 6 ሺህ ኩንታል ምርጥ ዘር በማቅረብ እየተሰራጨ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በምርት ዘመኑ የኩታ ገጠም አስተራረስንና የተሻሻሉ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም አርሶ አደሩን በምግብ ራሱን ለማስቻል የተያዘውን ግብ ለማሳካት እንደሚሰራም ገልጸዋል። ስነ-ምህዳርን መሰረት ያደረጉና የተሻሻሉ አምስት ዓይነት የሰብል ዝርያዎችን ለማቅረብ ዝግጅት ተደርጓል ያሉት ደግሞ የሰቆጣ ዝናብ አጠር ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር አዳነ ባህሩ (ዶ/ር) ናቸው። ማዕከሉ በምርት ዘመኑ በ80 ሄክታር መሬት ላይ የተሻሻሉ ዝርያዎችን የማባዛት ስራ እንደሚሰራ ጠቁመው በተጨማሪም ከ300 በላይ አርሶ አደሮች ማሳ ላይ የተሻሻሉ ዝርያ ያላቸው ሰብሎች ይለማሉ ብለዋል። የዝቋላ ወረዳ ግብርና ፅህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ተሾመ ስመኝ በበኩላቸው፤ በመጪው ክረምት ለአካባቢው ተስማሚ የሆኑ የእንቁ፣ የዳጉሳና የማሾ ሰብሎችን በኩታ ገጠም ለማልማት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የብሔረሰብ አስተዳደሩ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ የግብርና ባለሙያዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
የአዲስ አበባ ፈጣን ልማት እንግዶቿን በውበትና ታሪካዊ መስህቦቿ የምታስደምም የቱሪስት መዳረሻ እያደረጋት ነው 
Apr 29, 2026 72
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ፈጣን የዕድገት ጉዞ መዲናዋ የታላላቅ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁነቶች ማዕከል ብቻ ሳትሆን እንግዶቿን በውበትና ታሪካዊ መስህቦቿ የምታስደምም የቱሪስት መዳረሻም እያደረጋት መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ የቱሪዝም ኮሚሽን ገለጸ። በኢትዮጵያ ሀገራዊ ለውጥ ማግስት አዲስ አበባን እንደስሟ ውብና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ከተማ ለማድረግ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጨባጭ ውጤትን አስገኝተዋል። ለአብነትም በኮሪደር ልማት ከተማዋን ለሰው ልጅ ኑሮ ምቹ፣ ፅዱና ማራኪ በማድረግ ስሉጥ የእግረኛ፣ የብስክሌት፣ የመኪና መንገዶችን ጨምሮ አረንጓዴ መናፈሻ የልማት ሥራዎች ተገንብተዋል። በቱሪዝም ዘርፍም የብሔራዊ ቤተ-መንግስት ዕድሳት፣ የዓድዋ ድል መታሰቢያ፣ የገበታ ለሸገር ፕሮጀክቶችና የሳይንስ ሙዚየም የከተማዋን ገፅታ የቀየሩ ወሳኝ የልማት ስኬቶች ናቸው። በመሠረተ ልማትና ከተማ ውበትም የህንፃዎች ዕድሳት፣ የመንገድ መብራቶችና የዲጂታል ማስታወቂያዎች የከተማዋን ውበት የበለጠ እያደመቁት ይገኛል። የመዲናዋ ሁለንተናዊ የልማት ስኬትም የሀገር ውስጥና የዓለም አቀፍ የቱሪስት ፍሰትን በማሳደግ አዲስ አበባን የቱሪዝም ማዕከል እያደረጋት ነው። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር ሁንዴ ከበደ ለኢዜአ እንዳሉት፥ በአዲስ አበባ የተመዘገቡ ስኬታማ የለውጥ ሥራዎች መዲናዋን የመስህብ መዳረሻ እያደረጋት ነው። በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት ባለፉት ዘጠኝ ወራትም የሀገር ውስጥና የዓለም አቀፍ ጎብኝዎች ፍሰት በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። የአዲስ አበባ የቱሪስት ፍሰትም የቱሪዝም ዘርፍ በሀገር የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ የሚጠበቅበትን አዎንታዊ ሚና የሚያበረክትበትን ወሳኝ ዕድል እየፈጠረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ይህም የዜጎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚነት በማሳደግ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እንዲሻሻል እያደረገ መሆኑን አንስተዋል። በሌላ መልኩም የአዲስ አበባ አስደማሚ የለውጥ ሥራዎች መዲናዋን የአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የኮንፈረንስ ማዕከል መዳረሻ እያደረጋት እንደሚገኝ አስረድተዋል። አዲስ አበባ የታላላቅ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁነቶች ማዕከል ብቻ ሳትሆን እንግዶቿን በውበትና ታሪካዊ መስህቦቿ የምታስደምም የቱሪስት መዳረሻም ሆናለች ብለዋል። በአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ሁነቶች የሚሳተፉ እንግዶችም የመዲናዋን አስደማሚ ለውጥ በመጎብኘት የኢትዮጵያን ብሩህ ገፅታ ለዓለም በማስተዋወቅ የማይተካ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ለአብነትም ባለፉት ዘጠኝ ወራት ብቻ ከ200 በላይ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ኩነቶችን በስኬት በማስተናገድ በኮንፈረንስ ቱሪዝም ልማት ከፍተኛ ስኬት መገኘቱን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም