ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
የንግድ ምክር ቤቶችና ማህበራት ለህዝብ ያላቸውን ተደራሽነት በመጠቀም ለምክክሩ አሳታፊነትና አካታችነት ሚናቸውን መወጣት አለባቸው
Jun 17, 2026 566
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018(ኢዜአ)፦ የንግድ ምክር ቤቶችና ማህበራት ለህዝብ ያላቸውን ተደራሽነት በመጠቀም ለሀገራዊ ምክክሩ አካታችነትና አሳታፊነት ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባዬ ኦጋቶ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ከሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጋር በመተባበር "በሀገራዊ ምክክር ሂደት የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ" በሚል መሪ ሀሳብ በሀገራዊ ሰላምና መረጋጋት ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ አዘጋጅቷል፡፡   የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢ ለመፍጠር በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የግሉን ዘርፍ በመወከል ከመንግሥት ጋር ምክክር የሚያደርግ ተቋም ነው። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባዬ ኦጋቶ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የብዝሀነትና የዕምቅ አቅም ባለቤት ብትሆንም ለዘመናት ከግጭት አዙሪት መውጣት አቅቷት ቆይታለች። ስለሆነም የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዜጎች ያልተግባቡባቸውን ዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች በምክክር መፍታት የሚችሉበትን አውድ መፍጠሩን ገልጸዋል። ኮሚሽኑ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እንዲወያዩና ለችግሮች የጋራ መፍትሔ ለመፈለግ የተቋቋመ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት ኢትዮጵያውያን በነፃነት የሚነጋገሩበትን አውድ መፍጠር፣ የልዩነት መንስኤ የሆኑ አጀንዳዎችን መለየት እና በሂደቱ ላይ የሚወያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በመለየት ውጤታማ ሥራዎችን ማከናወኑን ገልጸዋል፡፡ የምክክር ሂደቱ ከጅምሩ አካታችና ሁሉን አቀፍ መሆኑን ገልጸው፤ ነጋዴዎችና የንግድ ተቋማት ባለቤቶች ከቀበሌ ጀምሮ እስከ ፌዴራል ድረስ በንቃት በመሳተፍ ሂደቱን ሲያሳልጡ ቆይተዋል ብለዋል፡፡ የንግድ ምክር ቤቶችና የንግዱ ማህበረሰብ ከተሳታፊነት ባለፈ በባለቤትነት ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ተናግረዋል፡፡ የንግድ ምክር ቤቶችና ማህበራት ለህዝብ ያላቸውን ተደራሽነት በመጠቀም ለሀገራዊ ምክክሩ አካታችነትና አሳታፊነት ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባም ነው የገለጹት፡፡ የንግዱ ማህበረሰብ የሰላምን፣ የመቻቻል፣ የመግባባትና የአንድነት ትርክት በመፍጠር አምባሳደር መሆን ይችላል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ከህዝብ ጋር ባላቸው ቀረቤታ ተግባራዊ ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡ የንግዱ ማህበረሰብ ለዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ከፍተኛ ሚና እንዳለው በመጥቀስ፣ በቀጣይ በዋናው የምክክር ጉባኤ ላይ የህዝቡን ተሳትፎ በማጎልበትና የባለቤትነት ሚናቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡   የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ዓይናለም አባይነህ (ዶ/ር)፤ በኢትዮጵያ ዘላቂነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት ለማስመዝገብ አስተማማኝ ሰላም ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የጀመረው ሂደት በኢትዮጵያ ለንግዱ ማህበረሰብ ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምህዳር መፍጠር እንደሚያስችልም ገልጸዋል፡፡ የንግዱ ማህበረሰብ የግሉን ዘርፍ በመወከል ለምክክር ሂደቱ ስኬት የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ ገልጸው፤ ምክክሮች ወደ ተጨባጭ ውጤቶች እንዲቀየሩ የበኩላቸውን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩም አረጋግጠዋል። የምክክር ኮሚሽኑ የጀመረው የምክክር ሂደት የጋራ እይታና የጋራ ልማት የሚያመጣ በመሆኑ ይህንኑ ጥረት በመደገፍ በንቃት እንደሚሳተፉ ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት እና የአማራ ክልል ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤቶች የቦርድ አባል እስማኤል አሊ፤ ችግሮችና አለመግባባቶች በውይይት ቢፈቱ የመጀመሪያው ተጠቃሚ የንግዱ ማህበረሰብ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እንደ ንግድ ማህበረሰብ ከቀበሌ ጀምሮ አጀንዳዎቻቸውን እያስያዙ በንቃት ሲሳተፉ እንደነበር ገልጸው፤ መወያየትና መመካከር ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ቦጋለ ቢታኒ በበኩላቸው፤ የምክክር ሂደቱ በሰፊው የተሳተፉበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የምክክር ኮሚሽኑ ሥራዎች የላቁ መሆናቸውን ገልጸው፤ የሰላሙ ባለቤት የሆነው የንግዱ ማህበረሰብ አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ ነው ብለዋል፡፡
የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ታሳቢ ያደረገው የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባሻገር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ነው
Jun 17, 2026 324
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018(ኢዜአ)፦የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ታሳቢ ያደረገው የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባሻገር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ነው ሲል በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የሕዝብ እና የባለድርሻ አካላት ይፋዊ የውይይት መድረክ አካሂዷል።   የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ላሌ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ግብርና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እድገት፣ የኢንዱስትሪ ልማት እና የሥራ ዕድል ፈጠራ ዋነኛ መሠረት ነው። ስለሆነም ኋላቀር ከሆነው የግብርና አሠራር በማላቀቅ ወደ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ እና ገበያ መር ሥርዓት ማሻገር እንደሚገባ ገልጸዋል። ይህ ረቂቅ አዋጅ ሲጸድቅ አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮች እና ከፊል አርሶ አደሮችን በኩባንያ በማደራጀት የመጠቀም መብታቸውን የሚያረጋግጥ ይሆናል ብለዋል። እንዲሁም የእንስሳት ሀብታቸውን እና ጉልበታቸውን ወደ ካፒታል በመለወጥ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የሚያስችል እንደሆነም ገልጸዋል።   የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ በዚሁ ወቅት፤ የግብርና ትራንስፎርሜሽንን ማረጋገጥ የመንግሥት ዋና ትኩረት በመሆኑ ለዚህም በርካታ የፖሊሲ፣ የፕሮግራም እና የተቋም ሪፎርም ሥራዎች በሀገር ደረጃ እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። ይህ ረቂቅ አዋጅ ግብርናን ለማሸጋገር ከሚከናወኑ የሪፎርም ሥራዎች መካከል ዋነኛው ሲሆን፤ አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ የሀገር ውስጥ ኩባንያዎችን እና ካምፓኒዎችን እንዲመሰርቱ ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡ አርብቶ አደሩን በማደራጀት፣ የእንስሳት ዝርያዎችን በማሻሻል እና የጤና አጠባበቅን በማዘመን፣ አርብቶ አደሩ የራንች ባለቤት እንዲሆንና ሥራዎቹን በባለቤትነት እንዲያከናውን ለማድረግ ታሳቢ ያደረገ ረቂቅ አዋጅ እንደሆነ ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ማንደፍሮ ንጉሤ እንደተናገሩት፤ ረቂቅ አዋጁ አርሶ አደሩን ወደ ኩባንያ አደረጃጀት በማሸጋገር የኢኮኖሚ እድገትን ይበልጥ ሊያፋጥኑ የሚችሉ አዳዲስ አቅሞችን መፍጠር ያስችላል ብለዋል። ሂደቱ አርሶ አደሮች ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን በምጣኔ ሀብት ከመደገፍ ባለፈ፤ በሀገሪቷ የኢኮኖሚ መዋቅር ውስጥ ግንባር ቀደም ተዋናይ እንዲሆኑ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ገልጸዋል። በመጪዎቹ አምስት እና አስር ዓመታት ውስጥ አርሶ አደሮቹን ወደ ከፍተኛ ደረጃ በማሸጋገር ድንበር ተሻጋሪ የንግድ ሥራዎችን የሚያከናውኑና በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ የሆኑ ትላልቅ የወጪ ንግድ ነጋዴዎች ይሆናሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። በውይይቱ የተሳተፉት ባለድርሻ አካላት ረቂቅ አዋጁ እንደሀገር የተያዘውን የገጠር ትራንስፎርሜሽን ከግብ የሚያደርስ ነው ብለዋል። አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ተጠቃሚ እና አሳታፊ የሆነ ሥርዓት እንደሚዘረጋ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል።  
በጅማ ዞን በሌማት ትሩፋት የተሰማሩ ወጣቶች ውጤታማ እየሆኑ ነው
Jun 17, 2026 313
ጅማ፣ሰኔ 10/2018(ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ጅማ ዞን በሌማት ትሩፋት የተሰማሩ ወጣቶች ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናገሩ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተተገበረ ጀምሮ በጅማ ዞን በርካታ ዜጎች ተጠቃሚ መሆን መቻላቸው ተገልጿል። መርሃ ግብሩ በተለይም ወጣቶች ከራስ አልፈው ለማህበረሰቡ የሚተርፍ ምርት እንዲያመርቱ ከማስቻሉም በላይ፣ የብዙዎችን የስራ አጥነት ችግር በዘላቂነት እየቀረፈ ይገኛል። በዞኑ ጮራ ቦቶር ወረዳ ነዋሪ የሆነው ወጣት አሸናፊ ባጊዴ እና ጓደኞቹ ተደራጅተው በዶሮ እርባታ ስራ ላይ በመሰማራት ውጤታማ መሆን የቻሉ ወጣቶች ናቸው። ወጣት አሸናፊ እንደሚያብራራው፣ ወጣቶቹ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ለረጅም ጊዜ ምንም አይነት የስራ እድል አላገኙም ነበር።   በመንግስት በተደረገላቸው ድጋፍ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ስር በዶሮ እርባታ የተሰማሩት እነዚህ ወጣቶች፤ በአሁኑ ወቅት በቀን ከሺህ በላይ እንቁላል ለገበያ እያቀረቡ ይገኛሉ። በዚህም በአጭር ጊዜ ውስጥ በመጀመሪያው ዙር ብቻ ከ100 ሺህ ብር በላይ መቆጠብ መቻላቸውን ገልጸዋል። ሌላኛው የዚሁ ወረዳ ነዋሪ የሆነው ወጣት አብዱላቂ አደም በሙዝ ልማት ላይ ተሰማርቶ ስኬታማ መሆን ችሏል። የግብርና ባለሙያዎች ያቀረቡለትን የተሻሻለ የሙዝ ዝርያና ሙያዊ እገዛ በመጠቀም፣ ምርቱን በስፋት ለገበያ እያቀረበ መሆኑን ተናግሯል። ከሚያገኘው ገቢ ራሱንና ቤተሰቡን ከመደገፍ ባለፈ፣ ለአራት የአካባቢው ወጣቶች ተጨማሪ የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልጿል። በሊሙ ኮሳ ወረዳ በዘንድሮው አመት በከብት ማድለብ ስራ ላይ የተሰማሩት ወጣት ሁሴን አባዱራ እና ጓደኛውም በተመሳሳይ ውጤታማ እየሆኑ መሆናቸውን ይናገራሉ። "ከዚህ ቀደም ምንም አይነት ስራ አልነበረንም፤ የከተማ አስተዳደሩ ባመቻቸልን የስራ እድል ተጠቅመን ወደ ስራ በመግባታችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ራሳችንን ችለን ለሌሎችም የስራ ዕድል መፍጠር ችለናል" ብለዋል።   የጅማ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም እንደገለጹት፤ በዞኑ በየአመቱ የሌማት ትሩፋት ተጠቃሚዎች ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መጥቷል። ዘርፉ ለበርካቶች የስራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ ማህበረሰቡ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ እያገዘ መሆኑን ጠቅሰው፤ በአሳ እና ከብት ዕርባታ፣ በንብ ማነብ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ምርት እንዲሁም በዶሮ እርባታ የመርሃ ግብሩ ዋና ዋና ዘርፎች ናቸው ብለዋል። በዞኑ በዘንድሮው አመት 314 ሺህ ሰዎችን የሌማት ትሩፋት ተሳታፊ ለማድረግ ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ እቅዱን በማሻገር ከ339 ሺህ በላይ ዜጎችን የመርሃ ግብሩ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የጽህፈት ቤት ኃላፊው ገልጸዋል።  
የቢሾፍቱ ከተማ የኮሪደር ልማት የህብረተሰቡን የአኗኗር ዘይቤ በተግባር ያዘመነና ተጠቃሚነትን ያረጋገጠ ነው
Jun 17, 2026 338
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018(ኢዜአ)፦ የቢሾፍቱ ከተማ የኮሪደር ልማት የህብረተሰቡን የአኗኗር ዘይቤ በተግባር የቀየረና ተጠቃሚነትን ያረጋገጠ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ገዛኸኝ ደጀኔ ገለጹ፡፡ ከተሞችን ምቹ የማድረግ፣ የማስዋብ እና የነዋሪዎችን ህይወት የማዘመን የኮሪደር ልማት መነሻ ከሆነችው አዲስ አበባ በቅርብ ርቀት የምትገኘው ቢሾፍቱ ፈለጓን በመከተል ላይ ትገኛለች።   የቢሾፍቱ ከተማ ምክትል ከንቲባ ገዛኸኝ ደጀኔ፤ ከተማዋን ለኑሮ ተመራጭ እና የቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ እቅድ ተይዞ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም በመጀመሪያው እና በሁለተኛው ዙር የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት አንድ መቶ አስራ ሰባት ኪሎ ሜትር የአስፋልት፣ የብስክሌትና የእግረኛ መንገዶች መገንባታቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለያዩ የከተማዋ ስፍራዎች ስማርት ፖሎች መተከላቸውን፣ የደህንነት ካሜራዎች መገጠማቸውን አንስተው ልዩ ልዩ ፓርኮች ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸውን ጠቁመዋል።   የኮሪደር ልማቱ ነዋሪዎች አካባቢያቸውን እንዲጠብቁ፣ ቆሻሻን በአግባቡ እንዲያስወግዱና ለአረንጓዴ ልማት ትኩረት እንዲሰጡ የአስተሳሰብ ለውጥ አምጥቷል ብለዋል። ንጹህ አየር፣ የመዝናኛ ስፍራዎችና የተስተካከለ የትራፊክ ፍሰት በመፈጠሩ የነዋሪዎች አካላዊና አእምሯዊ ጤንነት እንዲጠበቅ ማገዙንም አመላክተዋል። በኮሪደር ልማቱ 336 ሔክታር መሬት አረንጓዴ የማልበስ ስራ ተሰርቷል ነው ያሉት ምክትል ከንቲባው፡፡ በከተማዋ የተዘረጋው ዘመናዊ የኤሌክትሪክ አገልግሎት መስመርን ጨምሮ ሌሎች መሰረተ ልማቶች የ24 ሰዓት የንግድ እንቅስቃሴ እንዲኖር በማድረግ፤ የከተማዋን ገቢ በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደጋቸውን ተናግረዋል። ከተማዋ በገቢ ደረጃም በየዓመቱ 66 በመቶው እድገት እያስመዘገበች መምጣቷን ጠቁመው፤ ባለፉት አስራ አንድ ወራት ብቻ 14 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡን አስታውቀዋል።   በኮሪደር ልማቱና በሌሎችም ዘርፎች ለበርካታ የከተማዋ ነዋሪዎች በሥራ ዕድል ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን በማንሳት፥ እስካሁን ለ66 ሺህ ዜጎች በተለያዩ መስኮች ቋሚ የሥራ እድል ተፈጥሯል ብለዋል። የኮሪደር ልማት የህብረተሰቡን የአኗኗር ዘይቤ ያዘመኑና ተጠቃሚነትን ያረጋገጡ መሠረተ ልማቶችን እውን ያደረገ ነው ብለዋል፡፡ በከተማዋ ሦስተኛው ዙር የኮሪደር ልማት ተጠናክሮ መቀጠሉንም ምክትል ከንቲባው ጨምረው አስታውቀዋል።
በቀብሪ በያህ ከተማ በማህበር ተደራጅተው ሥራ የፈጠሩ ወጣቶች ውጤታማ ሆነዋል
Jun 17, 2026 163
ጅግጅጋ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል ፋፈን ዞን ቀብሪ በያህ ከተማ በማህበር ተደራጅተው ወደ ስራ የገቡ ወጣቶች ውጤታማ መሆናቸውን አስታወቁ። በሶማሌ ክልል ፋፈን ዞን ቀብሪ በያህ ከተማ፣ የስደተኞችና ተመላሾች አገልግሎት ከሒልተን ፋውንዴሽን ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ዐውደ ርዕይና ባዛር በመካሄድ ላይ ነው።   በዚህ ለሁለት ቀናት በሚቆየው ዐውደ ርዕይና ባዛር ላይ 20 የተደራጁ ማህበራት ምርቶቻቸውን ለገበያ አቅርበዋል። አብዲከሪን መሀመድ እና ጓደኞቹ በማህበር ተደራጅተው ከ500 በላይ ዶሮዎችን በማርባት የኢኮኖሚ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሥራውን ከጀመሩ ወዲህ ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ ለሌሎች ወገኖችም ድጋፍ ማድረግ መቻላቸውን ተናግረዋል። ማኅበሩ ከአካባቢው ማኅበረሰብና ከስደተኞች የተውጣጡ አባላት በጋራ የመሠረቱት መሆኑን ገልጸው፤በማህበር ተደራጅተን ስራ ከጀመርን ወዲህ ህይወታችን መለወጥ ችለናል ብለዋል።   አብዲ አህመድኑር እና ጓደኞቹም በማህበር ተደራጅተው ለከተማዋ የአትክልት ምርቶችን በማቅረብ ረገድ ተጠቃሚ ከሆኑት ወጣቶች መካከል ናቸው። በራሳቸው ከሚያመርቱት በተጨማሪም ከአምራች ገበሬዎችና ከአቅራቢዎች በመግዛት ለገበያ እንደሚያቀርቡ የገለጸው የማኅበሩ ሊቀመንበር ወጣት አብዲ አህመድኑር፤ ከሥራው ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቁሟል።   ወጣቶች በመደራጀትና ሥራ በመፍጠር ራሳቸውን ከመቻል ባለፈ፣ ለሌሎች ወገኖችም ድጋፍ መሆን እንደሚችሉ ገልፅዋል። በዐውደ ርዕዩ የተገኙት የኢፌዴሪ የስደተኞች እና ተመላሽ አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ብሩህተስፋ ሙሉጌታ እንደገለጹት፤ በቀብሪ በያህ ለሚገኙ ስደተኞች እና አስተናጋጅ ማህበረሰብ ማህበራዊና የኢኮኖሚ ትስስር በመፍጠር የጋራ ተጠቃሚነትን የማጠናከር ስራ እየተሰራ ነው።   የዐውደ ርዕዩ ዓላማ የስደተኞችንና የአካባቢውን ማኅበረሰብ የገበያ ትስስርና የንግድ እንቅስቃሴ ማጠናከር ሲሆን፣ ይህም የማኅበረሰቡን ኢኮኖሚያዊ ውህደትና ራስን የመቻል ጥረቶችን እንደሚያግዝ ገልጸዋል። በዚህም ዐውደ ርዕዩ ስደተኞችንና የአካባቢውን ማኅበረሰብ በአካታች የኢኮኖሚ ዕድሎች የሚያበረታታ መሆኑን ገልጸዋል።
ኮሌጁ የሌማት ትሩፋት ውጤታማነትን ለማጠናከር የበኩሉን እየተወጣ ነው
Jun 17, 2026 211
ሚዛን አማን፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የሌማት ትሩፋት ውጤታማነትን ለማጠናከር የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን የሚዛን ግብርና፣ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኮሌጅ ገለጸ። ኮሌጁ በሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ መሠረት እንቁላል፣ ወተት፣ ማር እና ዓሣ በብዛት አምርቶ ገቢውን ከማሳደግ ባለፈ ገበያን በማረጋጋት ማህበረሰቡን የማገልገል ግብ አስቀምጦ እየተንቀሳቀሰ መሆኑንም አስታውቋል። በኮሌጁ የቴክኖሎጂ ሽግግርና ኢንተርፕራይዝ ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ ጥላሁን አለማየሁ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ኮሌጁ ተማሪዎችን ከማሰልጠን በተጨማሪ ሀገራዊ ፖሊሲና ስትራቴጂዎችን መሠረት ያደረጉ የልማት ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል። ከዚህ ቀደም በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ላይ በስፋት ሲንቀሳቀስ እንደነበር አስታውሰው፣ ካለፉት ሦስት ዓመታት ወዲህም በሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቭ ላይ ውጤታማ ሥራ ለመስራት አቅዶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በአሁን ወቅት በኮሌጁ ከ9 ሺህ በላይ እንቁላል ጣይ ዶሮዎች እንዳሉ ገልጸው፣ ከእነዚህም በቀን በአማካይ ከ5 ሺህ በላይ እንቁላል እንደሚሰበሰብ ገልጸዋል። ይህም በከተማዋ የሚስተዋለውን የእንቁላል እጥረት ችግር በተወሰነ መንገድ መፍታቱን ገልጸው፣ በወተት ምርትም ተመሳሳይ ውጤት ለማስመዝገብ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል። ለእዚህም ከ50 በላይ ላሞችን መያዝ የሚችል ግንባታ እየተሰራ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ጥላሁን፣ በተመሳሳይ የሥጋ ዶሮ ለማርባት የሚያስችል ሼድም እየተዘጋጀ ነው ብለዋል። ከ300 በላይ የንብ ቀፎዎችን በማዘጋጀት የንብ ማነብ እና የዓሣ እርባታ ተግባራትም በዚህ ዓመት በኮሌጁ ትኩረት ተሰጥቷቸው እየተከናወኑ መሆኑን አቶ ጥላሁን አክለዋል። እንደ እሳቸው ገለጻ ኮሌጁ ምርት ከማምረት ባሻገር የተሻሻሉ ዝርያዎችን ለአርሶ አደሮች በማቅረብ ውጤታማ እንዲሆኑ እያገዘ ነው። በኮሌጁ የወተት እርባታ ፕሮጀክት ላይ የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው ወጣቶች መካከል ወጣት ታምራት አስራት እና መዓዛ ጥላሁን በገቢም በምርትም ተጠቃሚ እየሆንን ነው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት 15 የወተት ላሞችን በመንከባከብ፣ ወተት በማለብና ለሽያጭ በማዘጋጀት ሥራ በሚያገኙት ገቢ ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን እያስተዳደሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ሌላው የምርቱ ተጠቃሚ የሚዛን አማን ከተማ ነዋሪ አቶ እሰይ ኮንታ የሌማት ትሩፋት ሥራ በከተማዋ ከፍተኛ የእንቁላል ምርት እንዲኖር ማስቻሉን ገልጸው፣ ለዚህም ኮሌጁ የአንበሳውን ድርሻ ይይዛል ብለዋል። ለከተማው ነዋሪዎች በተመጣጣኝ ዋጋ እየቀረበ ያለውን የኮሌጁን የእንቁላልና የወተት ምርት ወስደው ልጆቻቸውን በመመገብ ጤናማና የተስተካከለ ዕድገት እንዲኖራቸው እያደረጉ መሆኑንም ተናግረዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን የስንዴ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 17, 2026 212
ነገሌ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ቦረና ዞን በበልግ አዝመራ የስንዴ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ ትኩረት መሰጠቱን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ሊበን ቦሩ፤ በዞኑ በልግ አዝመራ 176 ሺህ 223 ሄክታር መሬት በስንዴ፣ ጤፍ፣ ቦለቄ እና ቦቆሎ መልማቱንም አስታውቀዋል፡፡ ከዚህም ውስጥ 61 ሺህ 643 ሄክታር መሬት በስንዴ ልማት በመሸፈን የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።   በስንዴ ልማቱ የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግም የተሻሻሉ የግብርና አሰራሮችን ከመተግበር ባለፈ ምርጥ ዘርና የአፈር ማዳበሪያ በወቅቱ ለአርሶ አደሩ እንዲቀርብ ተደርጓል ብለዋል። በዞኑ በስንዴ ልማት ከተሸፈነው መሬት አብዛኛው በኩታ ገጠም የለማና በመስመር የተዘራ በመሆኑ ሰብሉ በአሁኑ ወቅት በጥሩ ቁመና ላይ ይገኛል ብለዋል። በዞኑ ከ42ሺህ 130 በላይ አርሶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮችን በማሳተፍ በስንዴ ከለማው ማሳ 1 ሚሊዮን 365 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅም አስታውቀዋል፡፡ በዞኑ አርሶ አደሮች እና ከፊል አርብቶ አደሮችን ከእርዳታ ጠባቂነት ወደ ምርታማነት ለማሸጋገር የግብርና አሰራርን ለማዘመን እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፣ የባለሙያ ድጋፍም መደረጉንም ገልጸዋል። በበልግ እርሻ ከተሳተፉ አርሶ አደሮች መካከል በዞኑ ሊበን ወረዳ የጎቢቻ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አብዲ ኑር እንዳሉት የተሻሻለ የግብርና አሰራርን በመጠቀም በሦስት ሄክታር መሬታቸውን ላይ ስንዴ አልምተዋል።   በስንዴ ልማቱን ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር የኩታ ገጠም አስተራረስ ዘዴ መከተላቸውና የተስተካከለ የዝናብ ስርጭት መኖሩ ስራቸውን ውጤታማ እንደሚያደርገው ተናግረዋል፡፡ ወረዳው ምርጥ ዘር፣ ማዳበሪያ እንዲሁም ትራክተር በወቅቱ ማቅረቡ ስራቸውን በተገቢው ለማከናወን እንዳስቻላቸውም ጠቁመዋል። የእዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ወርቁ አለባቸው በበልግ ወቅት በስንዴ ካለሙት ሦስት ሄክታር መሬት የተሻለ ምርት እንደሚያገኙ ተስፋ ማድርጋቸውን ተናግረዋል።   በግብርና ባለሙያ ድጋፍ ታግዘው ያከናወኑት የስንዴ ልማት በጥሩ ሁኔታ ላይ መገኘቱ የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥ እንደሚያስችላቸው ገልጸዋል። በምስራቅ ቦረና ዞን ከመጋቢት አጋማሽ እስከ ሚያዚያ የዝናብና የዘር ወቅት ሲሆን ከሐምሌ አጋማሽ እስከ ነሀሴ የምርት መሰብሰቢያ ወቅት መሆኑን ከዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የተገኘ መረጃ ያሳያል፡፡
የሀረሪ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት (ካቢኔ) የቀረበለትን የበጀት ክለሳ አፀደቀ
Jun 17, 2026 120
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ) ፦ የሀረሪ ክልል መስተዳድር ምክር ቤት (ካቢኔ) ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ የ2018 የበጀት አመት የ11 ወራት እቅድ አፈጻጸም መነሻ በማድረግ የቀረበለት የበጀት ክለሳ አፅድቋል። ካቢኔው በክልሉ ገንዘብና ኢኮኖሚ ትብብር ቢሮ አማካኝነት የቀረበለትን ከ301 ሚሊየን 693 ሺህ 178 ብር የበጀት ክለሳ ነው ተወያይቶ ያፀደቀው። የበጀት ክለሳው በተለይም የፊዚካልና ፋይናንሻል አፈፃፀማቸው ዝቅተኛ የሆኑ ፕሮጀክቶችን በመለየት የላቀ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ፋይዳ ላላቸውና የበጀት እጥረት ላጋጠማቸው ጉዳዮች የሚውል ነው ተብሏል።   አፈፃፀማቸው ዝቅተኛ የሆኑ ፕሮጀክቶችን በመለየትና በመከለስ የቅድሚያ ቅድሚያ ለተሰጣቸው ተግባራት በቀሪው የበጀት ዓመቱ ጊዜ የሚውል መሆኑም ተመልክቷል። ካቢኔውም የቀረበለትን የበጀት ክለሳ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል። የክልሉ ካቢኔ ከዚህ በተጨማሪም በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ አቅጣጫ ማስቀመጡን ኢዜአ ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
አርሶ አደሮች ከሰብል ልማት በተጓዳኝ ቀይ ሽንኩርት በማምረት ተጠቃሚ ሆነዋል
Jun 17, 2026 123
ጭሮ ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ከሰብል ልማት በተጓዳኝ በቀይ ሽንኩርት ማምረት ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆናቸውን የምዕራብ ሐረርጌ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ ከ26 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በበልግ እርሻ ቀይ ሽንኩርትን በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን የገለጸው ደግሞ የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ፅህፈት ቤት ነው። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የገመቺስ ወረዳ አርሶ አደሮች እንደገለጹት፤ በመደበኛው የበልግ አዝመራ በዋናነት ከሚያለሙት የእህል ሰብል በተጓዳኝ ቀይ ሽንኩርት በማልማት ከፍተኛ ገቢ እያገኙ ነው። በወረዳው ቁኒ ሶገሪያ ቀበሌ አርሶ አደር አብዮት ሽመልስ ፤ ቀደም ሲል በበልግ እርሻ የምግብ ሰብል ምርት ላይ ብቻ ተወስነው የቆዩ ቢሆንም አሁን ላይ ሽንኩርት ማምረታቸውን ገልጸዋል።   ባለፈው መኸር ግማሽ ሄክታር በሚጠጋ ማሳ ላይ ያለሙትን 50 ኩንታል ሽንኩርት ለገበያ በማቅረብ ከ280 ሺህ ብር በላይ ገቢ በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከዘርፉ እያገኙ ባለው ገቢም ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ በበቂ መጠን ገዝተው ከመጠቀም ባለፈ ጥሪት ለማፍራት መቻላቸውን አስረድተዋል። በተያዘው የመኸር ወቅት እርሻም ከሌሎች ሰብሎች ጋር በጥምር ልማቱን በማስፋፋት ላይ መሆናቸውን የተናገሩት አርሶ አደሩ እስከ 80 ኩንታል ምርት እንደሚጠብቁም ገልፀዋል። ሌላኛው አርሶ አደር ፀጋዬ ታረቀኝ በበኩላቸው፤ የሽንኩርት ምርት ገበያ ላይ ተፈላጊ ከመሆኑም ባለፈ ነጋዴዎች አካባቢያቸው ድረስ መጥተው ምርታቸውን ስለሚረከቡ የስራ ተነሳሽነታቸው መጨመሩን ተናግረዋል።   ከልማቱ በሚያገኙት ገቢ የሰብል ልማታቸውን ከማስፋፋት ባለፈ የቀንድ ከብት ገዝተው በማድለብ ገቢያቸውን ለማሳደግ አቅም እንደፈጠረላቸው አስረድተዋል። ባለፈው በልግ ወቅት 35 ኩንታል ምርት ለገበያ በማቅረብ ከ170 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት ምርጥ ዘርና ማዳበሪያን በመጠቀም ምርታማነታቸውን ለማሳደግ በትኩረት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። የምዕራብ ሐረርጌ ዞን እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ፅህፈት ቤት የሰብል ልማት አስተባባሪ አቶ መደቅሳ ዴሬሳ ፤በዞኑ 15 ወረዳዎች በበልግ አዝመራ 5 ሺህ 535 ሄክታር የሚሆን መሬት በቀይ ሽንኩርት መልማቱን ገልፀዋል።   በልማቱም ከ26 ሺህ 270 በላይ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ መሆኑን ጠቅሰው ውጤታማ እንዲሆኑ በግብርና ባለሙያዎች የቅርብ ድጋፍና እገዛ እየተደረገላቸው መሆኑን ተናግረዋል። ለልማቱ ስኬታማነት 2 ሺህ 212 ኩንታል ማዳበሪያ እና 144 ኩንታል የሽንኩርት ምርጥ ዘር መቅረቡን ጠቁመዋል። በዞኑ እየተካሄደ ባለው የሽንኩርት ልማት ከ770 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ይገኛል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስታውቀዋል።
በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ የተመረተ 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ቶን ቡና ለማዕከላዊ ገበያ እየቀረበ ነው
Jun 17, 2026 180
አዳማ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ በተደረገ እንቅስቃሴ 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ቶን ቡና ተመርቶ ለማዕከላዊ ገበያ እየቀረበ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የቡናና ፍራፍሬ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መሀመድ ሳኒ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ የቡና ልማት ለአርሶ አደሩ የኢኮኖሚ ምንጭነት ጉልህ አስተዋጽኦ እያደረገ ነው። ይህንን አጠናክሮ ለማስቀጠል የቡና ማሳን በማሳደግ ልማቱን ከማስፋፋት ባለፈ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች ለአርሶ አደሮች ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህ በተጨማሪ የተሻሻሉ ግብዓቶችና የተፈጥሮ ማዳበሪያ በአግባቡ የመጠቀም፣ የቡና ጥላ ዛፎችን የማልማት እና ያረጁ የቡና ተክሎችን የመጎንደል ሥራ ሲሰራ መቆየቱን ጠቅሰዋል። አርሶ አደሩም የድህረ-ምርት አያያዝ ቴክኖሎጂዎችን በአግባቡ እንዲጠቀምና በቡና ልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን እንዲያሳድግ በየደረጃው የተቀናጀ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በዘንድሮ የምርት ዘመን 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን ቶን ቡና በክልሉ ለማምረት ታቅዶ እስከ ግንቦት 30 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ዕቅዱን ሙሉ ለሙሉ ማሳካት ተችሏል ብለዋል። እንደ ኃላፊው ገለጻ የታጠበ ቡና እና ደርቆ የተቀሸረ ቡናን ለማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ ሲሰራ የቆየ ሲሆን፣ እስካሁንም ከ350 ሺህ ቶን በላይ ምርት ለማቅረብ ተችሏል። ከክልሉ ለውጭ ገበያ የሚቀርበው የቡና ምርት ጥራትና ደረጃውን የጠበቀ እንዲሆን ለማድረግ በተሰጠው ትኩረት ከአርሶ አደሩ ማሳ ጀምሮ የቡና ምርት ጥራቱን ጠብቆ እንዲለቀም መደረጉንም ተናግረዋል።   በክልሉ በቡና ልማት ከሚታወቁ አካባቢዎች መካከል የጅማ ዞን አንዱ ሲሆን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሚፍታህ ገቢ በሰጡት አስተያየት፤ በዞኑ በ600 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ልማት እየተከናወነ ይገኛል። የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የክልሉ መንግሥት የነደፋቸውን አዳዲስ የቡና ኢኒሼቲቮች በቡና ልማት ለተሰማሩ አካላት የማስተዋወቅ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ በማድረግ እና ዘመናዊ አሰራሮችን በመተግበር ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን ነው የገለጹት። በዚህም በዞኑ የቡና ምርታማነትን በአማካይ በሄክታር 11 ኩንታል ማድረስ መቻሉን አቶ ሚፍታህ ተናግረዋል። በዞኑ በዚህ ዓመት በምርት አሰባሰብ ሒደት የአርሶ አደሩን ግንዛቤ በማሳደግ ጥራቱን የጠበቀ ቡና ለማዕከላዊ ገበያ ለማቅረብ በተሰራው ሥራ እስካሁን ድረስ 41 ሺህ 569 ቶን ቡና መመረቱንም አመልክተዋል።
የእንግሊዝ መንግሥት የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን ያደረገው የቴክኖሎጂ ድጋፍ የጋራ ደኅንነትን ለማረጋገጥ ያግዛል
Jun 16, 2026 1059
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018(ኢዜአ)፦ የእንግሊዝ መንግሥት የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን ያደረገው የቴክኖሎጂ ድጋፍ የጋራ ደኅንነትን ለማረጋገጥ እንደሚያግዝ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) ገለጹ። የእንግሊዝ መንግሥት የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን ያደረገው 25 ሚሊየን ብር የሚያወጣ የቴክኖሎጂ እገዛ የርክክብ መርሐ-ግብር እና ጉብኝት በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የአቪዬሽን ደኅንነት ዋና መምሪያ መከናወኑን አገልግሎቱ ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መረጃ አመልክቷል።   በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ዳረን ዌልች የተመራ ልዑክ እንዲሁም የኢትዮጵያ አየር መንገድና የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት መርሐ-ግብር ላይ የአገልግሎቱ ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል ሲሳይ ቶላ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ድጋፉ በኢትዮጵያና በእንግሊዝ መካከል ያለውን ትብብርና የጋራ ደኅንነትን የማረጋገጥ አጋርነት ማሳያ ነው። መርሐ-ግብሩ በኢትዮጵያና በእንግሊዝ መካከል ያለውን ዘላቂ አጋርነት የሚያሳይ ወሳኝ ምዕራፍ መሆኑን ጠቁመው፤ የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን የተደረገው የቴክኖሎጂ ድጋፍ በትብብር ስንሰራ በጋራ ደኅንነትና በዓለም አቀፍ ትስስር አውድ የምናሳካቸውን ድሎች ያሳያል ብለዋል። የአቪዬሽን ደኅንነት ስጋት ተለዋዋጭና በየጊዜው እያደገ የሚመጣ የዘርፉ ፈተና ነው። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ ያለውን የበላይነት አስጠብቆ ለመዝለቅ የደኅንነት ስጋቶችን አስቀድሞ በማወቅ ማስቀረት ወሳኝ ተልዕኳች ነው ያሉት ዶ/ር ሲሳይ፤ የቴክኖሎጂ ድጋፉ የመፈጸም አቅምን ያሳድጋል ሲሉ ተናግረዋል።   ኢትዮጵያና እንግሊዝ ትብብራቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቁመው፤ በተለይ በቢሾፍቱ የሚገነባው አዲሱ የአየር ማረፊያና ሀገሪቱ እ.አ.አ በ2027 የምታስተናግደው የኮፕ-32 ጉባኤ በተለያዩ የአጋርነት ማዕቀፎች የሚገለጹ ወሳኝ ሁነቶች መሆናቸውን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በዓመት እስከ 120 ሚልየን መንገደኞችን የሚያስተናግድ በአፍሪካ ግዙፍ የሆነ አየር ማረፊያ እየገነባች መሆኑን አመልክተው፤ ይህ ከአቪዬሽን ደኅንነት አኳያ ከፍተኛ ዝግጁነት እንደሚፈልግ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ዳረን ዌልች በበኩላቸው፤ ሁለቱ ሀገራት እስከ ዛሬ የዘለቀና ጠንካራ ወዳጅነት እንዳላቸው ጠቁመዋል። የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን የተደረገው እገዛ ይህንኑ የሚመሰክርና የሚያጠናክር መሆኑንም አመልክተው ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ደኅንነት ዘርፍ ያላት ቁመና የሚደነቅ መሆኑንም መስክረዋል። በየእለቱ የምታከናውኑት ተግባር የሀገሪቱንም የእኛንም ደኅንነት ስለሚያረጋግጥ አድናቆቴን መግለጽ እወዳለሁ ያሉት አምባሳደሩ የቦሌ ዓለም-አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ቁልፍ የሆነ የዓለም-አቀፍ ተጓዞች መዳረሻና ማዕከል ነው፡፡ ደኅንነትን የማረጋገጥ ጉዳይ የሁላችንም የጋራ ኃላፊነት መሆኑ ይታወቃል ብለዋል።   በዓለም አቀፍ ደረጃ እየተከሰቱ ያሉ የበረራ ደኅንነት ስጋቶችን ለመቀነስ ዘመናዊ መሣሪያዎችን መታጠቅ መፍትሔ ስለሚሆን በአፍሪካ ለመጀመሪያ ጊዜ ስራ ላይ የሚውል ዘመናዊ ቴክኖሎጂ ለኢትዮጵያ መበርከቱንም ተናግረዋል። የአቪዬሽን ደኅንነት ዋና መምሪያ ዳይሬክተር አስራት ቀጄላ፤ ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ደኅንነት ዘርፍ ዓለም-አቀፍ መመዘኛዎችን በብቃት በማሟላት ተጠቃሽ ሀገር መሆኗን አረጋግጠዋል። የእንግሊዝ መንግሥት ድጋፍም በተለያየ መንገድ ሲገለጽ መቆየቱን አመልክተው፤ ለተደረገው እገዛም ምስጋና አቅርበዋል። ከእንግሊዝ መንግሥት ጋር በተለያዩ የተቋማዊ ግንባታ መስኮች ዘርፈ ብዙ ትብብሮችን ስናደርግ ቆይተናል ይህም ለኢቪዬሽንና ለዓለም-አቀፍ አየር ትራንስፖርት ዘርፍ ደኅንነት መረጋገጥ ጉልህ ሚና ወደ ሚያበረክት ስትራቴጂክ ምዕራፍ ተሸጋግሯል ሲሉም ገልጸዋል። የአቪዬሽን ዘርፉን ለማዘመን የተደረገው ድጋፍ ዘመኑን የዋጀ የበረራ ደኅንነትን ለማከናወን ከፍተኛ ሚና እንደሚያበረክት አቶ አስራት አመልክተዋል። በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ በኩል የተደረገው ድጋፍ ከሀገሪቱ ‹‹ሆም ኦፊስ ኢንተርናሽናል ኦፕሬሽን›› ቢሮ የተገኘ መሆኑን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለመገናኛ ብዙኃን የላከው መረጃ ጠቁሟል።
የቱሪዝም ዘርፉን በዲጂታል ቴክኖሎጂ ለማዘመን እየተሰራ ነው
Jun 16, 2026 315
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዲጂታል ቴክኖሎጂ አማራጮችን በመጠቀም የቱሪዝም ዘርፉን ለማዘመን እየሰራች መሆኑን የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስትር ዴኤታው ከዓለም አቀፉ የብራንዲንግ እና ሚዲያ ተቋም "FAME by Sheeraz" መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ ሺራዝ ሀሰን እና የልዑካን ቡድናቸው ጋር በቱሪዝም ዘርፍ በትብብር መስራት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል። እንደገና አበበ (ዶ/ር) መንግስት ባለፉት ስምንት ዓመታት አዳዲስ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በመገንባት፣ ነባሮቹን በማደስ እና የዲጂታል ቴክኖሎጂን (Visit Ethiopia Portal) በመጠቀም ዘርፉን ለማዘመን እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም አዲስ አበባን የአህጉሪቱ የኮንፈረንስ ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ እየተደረገ ያለውን ጥረት ጠቅሰው፤ እንደ "FAME by Sheeraz" ባሉ ተቋማት አማካኝነት የኢትዮጵያን የቱሪዝም ሀብቶች በዓለም አቀፍ ደረጃ ማስተዋወቅ አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል። የ"FAME by Sheeraz" መስራች ሺራዝ ሀሰን በበኩላቸው፣ ድርጅታቸው በአሜሪካ፣ በአውሮፓ እና በመካከለኛው ምስራቅ ታዋቂ ግለሰቦችን እና የንግድ ምልክቶችን በማስተሳሰር የረጅም ጊዜ ልምድ እንዳለው ገልጸዋል። ይህንን ልምድ በመጠቀም የኢትዮጵያን ገጽታ ለመገንባት በጋራ ለመስራት ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላቸው የገለጹት ዋና ስራ አስኪያጁ፤ ለተግባራዊነቱም ተቋሙ በአዲስ አበባ ቋሚ ጽሕፈት ቤት እንደሚከፍት ጠቁመዋል። በተጨማሪም በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) የታገዙ የመገናኛ ብዙኃን አማራጮችን በመጠቀም ኢትዮጵያን በአፍሪካ ቀዳሚ የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግ ስትራቴጂያዊ እቅድ ቀርጸው ለመንቀሳቀስ ዝግጁ መሆናቸውን ነው ዋና ስራ አስኪያጁ ያረጋገጡት። በውይይቱ ወቅት፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል የተነሱትን ነጥቦች ወደ ተግባር ለመቀየር ስምምነት ላይ መደረሱን የቱሪዝም ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
የከተማዋ እድገት ተደማሪና ቀጣይነት ያለው እንዲሆን አመራሩ በቁርጠኝነትና በተደራጀ መንገድ ሊመራ ይገባል
Jun 16, 2026 1007
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-የአዲስ አበባ ከተማ እድገት ሁልጊዜም ተደማሪና ቀጣይነት ያለው እንዲሆን አመራሩ በቁርጠኝነትና በተደራጀ መንገድ ሊመራ እንደሚገባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ በቀጣዮቹ 90 ቀናት መሪ ዕቅድ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ አካሂዷል።   የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ ባለፉት ጊዜያት የተመዘገቡ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠልና በከተማዋ የተጀመሩ ግዙፍ የልማትና የሪፎርም ሥራዎችን በላቀ ፍጥነት ለማጠናቀቅ የ90 ቀናት መሪ ዕቅዱ ሚና የጎላ ነው ብለዋል። ዕቅዱ በዋናነት የሕዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ፣ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን መፍታት፣ አገልግሎት የማሻሻል ስራን በማጠናከር የመሶብ አንድ ማእከል ዲጂታል አገልግሎትን ማስፋት፣ የኑሮ ውድነትን ማረጋጋት፣ የንግድ ስርዓቱን መግራት፣ የስራ እድል ፈጠራ እና የወጣቶችና ሴቶች ተጠቃሚነት ላይ መስራት ነው ብለዋል። እንዲሁም የአረንጓዴ አሻራ ልማት፣ የከተማ ግብርና እና የሌማት ትሩፋት፣ የሰላም ግንባታ ስራዎች፣ የገቢ አሰባሰብ፣ ልመናንና ተረጂነትን መቀነስ፣ የበጎ ፈቃድ መርሃ ግብርን በተቀናጀ የህብረተሰብ ተሳትፎ መተግበር፣ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄን በአዲስ ቅኝት መምራት እና ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶችን ማጠናቀቅ የእቅዱ አካል መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የተጀመሩ የኮሪደር ልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎችን በጥራት እና በተያዘላቸው የጊዜና በጀት ማጠናቀቅ እና የሚዲያና የህዝብ ግንኙነት ስራዎችን ለማጠናከር መታቀዱን ተናግረዋል። የታቀዱ ግቦችን ለማሳካት በየደረጃው የሚገኘው አመራር በቁርጠኝነትና በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት መሥራት እንደሚኖርበትም አጽንኦት ሰጥተዋል። በመድረኩ ላይ የቀረቡት የመንግሥትና የፓርቲ ዕቅዶች ከተማዋን ምቹ፣ ፅዱና ዘመናዊ የማድረግ ራዕይን መሠረት ማድረጋቸውንም ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገልጸዋል። የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብና ጥራት እንዲጠናቀቁ የሚያስችሉ በመሆናቸው ለዕቅዶቹ መሳካት መትጋት እንደሚገባ ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃንጥራር አባይ በበኩላቸው፤ በመጪዎቹ ሦስት ወራት አመራሩ በተሟላ አግባብ ለሕዝብ ቁርጠኛ አገልግሎት የሚሰጥበት ጊዜ መሆን እንዳለበት ገልጸዋል።   ከተማዋ በአሁኑ ወቅት እጅግ በርካታና ዕረፍት የሚነሱ ሥራዎች ያሉባት መሆኑን ገልጸው፤ ይህንንም አመራሩ ሊገነዘብ እንደሚገባም አሳስበዋል። በክረምቱ ወቅት የሚከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ፣ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ ከወትሮው አገልግሎት ውጭ ያሉ የመሠረተ ልማት ግንባታዎች እና የፕሮጀክት ክዋኔዎች ከፍተኛ ትኩረት የሚሹ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለዚህም አመራሩ ፕሮጀክቶችን ከተቀመጠላቸው ጊዜ ቀድሞ ለማጠናቀቅ የሚያስችል ከፍተኛ ተነሳሽነትን ማጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል።   በብልፅግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ ፤ በቀጣዮቹ ቀናት በአመራሩና በመዋቅሩ ውስጥ አዲስ የሥራ ተነሳሽነትና ጥንካሬ መፈጠር እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል። አሁን መዋቅሩንና አመራሩን በከፍተኛ ደረጃ በማነቃቃት እንዲሁም አባላትን በማስተባበር በ90 ቀናቶቹ የታቀዱት ሥራዎች ላይ የተጠናከረ የሥራ አፈጻጸም ማምጣት እንደሚገባና ለዚህም ዝግጁነትን አጠናክሮ መሄድ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።
ቡናን በበጋ መስኖ በማልማት የአምራቹን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት ተደርጓል
Jun 16, 2026 219
አዳማ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ቡናን ከመደበኛ ወቅት በተጨማሪ በበጋ መስኖ በማልማት የአምራቹን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ትኩረት መደረጉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው የክልሉን የቡና ምርትና ምርታማነትን በበጋ መስኖ ለማስፋፋት ያዘጋጀው የባለሙያዎችና አመራሮች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና መድረክ በአዳማ እየተካሄደ ይገኛል።   የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ መሀመድ ሳኒ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ አዲስ የቡና፣ ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ኢኒሼቲቭ ፓኬጅ ተቀርጾ ተግባራዊ እየተደረገ ነው። የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ ልማቱን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ፣ ከአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖ ጋር እያጋጠመ ያለውን የቡና ተባይና በሽታን ለመቋቋም የሚያስችል ስትራቴጂ ተነድፎ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተያዘው ስትራቴጂ ላይ ግንዛቤ እንዲፈጠር ለባለሙያዎችና ለአመራሮች ስልጠናው መዘጋጀቱን አመልክተዋል። በዚህ ረገድ በክልሉ በጥቂት ባለሀብቶች የተጀመረውንና ውጤት የተገኘበትን የበጋ መስኖ ቡና ልማት ተሞክሮ በመቀመር ወደ አርሶ አደሩ ለማስፋፋት አቅጣጫ መያዙን አስታውቀዋል። ለዚህም በየደረጃው ለሚገኙ አርሶ አደሮች የክህሎት ስልጠና በመስጠት እና የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ማዳበሪያን በማመጣጠን የቡና መስኖ ልማትን ለማስፋፋት እንደሚሰራ ገልጸዋል። በዚህም አሁን ላይ በክልሉ ከአንድ ሄክታር ላይ የሚገኘውን ዘጠኝ ኩንታል ምርት ወደ 20 ኩንታል ለማሳደግ ግብ መያዙን አብራርተዋል። በቀጣይም እስከ ቀበሌ ድረስ ስልጠናዎችን በመስጠት እና የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመትከል እንዲሁም የቡና ልማትን በኩታገጠም እንዲታረስ በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ተፈጻሚ እንደሚደረግ አስረድተዋል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ተሾመ ቦጋለ በበኩላቸው፤ ቡናን በመስኖ በማልማት በሄክታር ከ30 እስከ 40 ኩንታል ምርት ማግኘት እንደሚቻል ገልጸዋል። ይህ ብቻ ሳይሆን በቂ ሙያዊ ድጋፍ ከተደረገ በዓመት ሁለት ጊዜ ምርት እንደሚሰጥም ተረጋግጧል ብለዋል።   በመሆኑም አርሶ አደሩ ያረጁ የቡና ዝርያዎችን በተሻሻሉ ዝርያዎች በመተካት እና በቂ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ማዳበሪያን በማመጣጠን ምርታማነቱን እንዲያሳድግ ኢንስቲትዩቱ ቴክኖሎጂ የማስተዋወቅ ስራ እየሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። እውቀት፣ ክህሎት፣ ቴክኖሎጂ እና የተፈጥሮ ጸጋን በማቀናጀት በጥቂት ዓመታት ውስጥ የቡና ምርታማነትን ከእጥፍ በላይ በማሳደግ ዘርፉ ለውጭ ምንዛሪ ግኝቱ የላቀ አስተዋጽኦ ማበርከት እንደሚቻልም አረጋግጠዋል። ለአራት ቀናት በተዘጋጀው የአሰልጣኞች ስልጠና መድረክ ላይ ከክልሉ ሁሉም አካባቢዎች የተውጣጡ ከ1 ሺህ 500 የሚበልጡ የግብርና ባለሙያዎችና አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
 በቀጣዮቹ 90 ቀናት የመዲናዋን ነዋሪዎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ላይ ትኩረት ተደርጎ ይሠራል
Jun 16, 2026 180
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቀጣዮቹ 90 ቀናት የከተማዋን ነዋሪዎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ላይ በትኩረት እንደሚሠራ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ በቀጣዮቹ 90 ቀናት መሪ ዕቅድ ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ አካሂዷል።   የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ ባለፉት ጊዜያት የተመዘገቡ ስኬቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠልና በከተማዋ የተጀመሩ ግዙፍ የልማትና የሪፎርም ሥራዎችን በላቀ ፍጥነት ለማጠናቀቅ የ90 ቀናት መሪ ዕቅዱ ሚና የጎላ ነው ብለዋል። ዕቅዱ በዋናነት የሕዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የኮሪደር ልማት፣ የገቢ መሰብሰብ፣ የአረንጓዴ ዐሻራ፣ የኑሮ ውድነት ማቃለል፣ የሥራ ዕድል ፈጠራ፣ የክረምት በጎፈቃድ እና በመሶብ አንድ ማዕከል የሚሰጡ አገልግሎቶች ማብዛት እና ሌሎች ስትራቴጂካዊ ተግባራት ላይ ትኩረት ማድረጉን ጠቁመዋል። እንዲሁም የከተማ ግብርና፣ የሌማት ትሩፋት፣ የትምህርት ዘርፍ ማጠቃለያ እና የዝግጅት ምዕራፍ፣ የጎርፍ መከላከል ሥራ በትኩረት እንደሚከናወኑም አንስተዋል።   የታቀዱ ግቦችን ለማሳካት በየደረጃው የሚገኘው አመራር በቁርጠኝነትና በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት መሥራት እንደሚኖርበትም አጽንኦት ሰጥተዋል። በመድረኩ ላይ የቀረቡት የመንግሥትና የፓርቲ ዕቅዶች ከተማዋን ምቹ፣ ፅዱና ዘመናዊ የማድረግ ራዕይን መሠረት ማድረጋቸውንም ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገልጸዋል። የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች በተቀመጠላቸው የጊዜ ገደብና ጥራት እንዲጠናቀቁ የሚያስችሉ በመሆናቸው ለዕቅዶቹ መሳካት መትጋት እንደሚገባ ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን ሰብስቧል
Jun 16, 2026 181
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን መሰብሰቡን የፈንዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ደሳለኝ አምባው (ዶ/ር) አስታወቁ፡፡ የፈንዱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ደሳለኝ አምባው (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የመድን ፈንዱ በተቋቋመ አጭር ዓመታት ውስጥ ለአባል የፋይናንስ ተቋማት አማራጭና ውጤታማ የፋይናንስ ሥርዓት ፈጥሯል። ከአባል ፋይናንስ ተቋማት አርቦን መሰብሰብ፣ የተሰበሰበን አርቦን በመንግስት ግምጃ ቤት ሰነድ ኢንቨስትመንትን ማሳደግና አንድ የፋይናንስ ተቋም ቢወድቅ ተቋሙን በመተካት ለገንዘብ አስቀማጮች ከ90 ቀናት ባነሰ ጊዜ መክፈል የሚያስችሉ ዋና ዋና ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በዚህም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ጨምሮ ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ ውጭ ሁሉም የግል ባንኮችና ሁሉም የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ አባል መሆናቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከተቋቋመ ጀምሮ እስካሁን ባለው ከአባል የፋይናንስ ተቋማት 20 ነጥብ 61 ቢሊየን ብር አረቦን መሰብሰቡን አስታውቀዋል። ከዚህ ውስጥ 18 ነጥብ 72 ቢሊዮን ብር ከመደበኛ ተቀማጭ ገንዘብ የተሰበሰበ ሲሆን፤ ቀሪው 1 ነጥብ 89 ቢሊዮን ብር ደግሞ ከወለድ ነጻ ተቀማጭ ገንዘብ የተሰበሰበ መሆኑን አስረድተዋል። የፈንዱ አጠቃላይ የኢንቨስትመንት ክምችትም ካለፈው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የ89 ነጥብ 76 በመቶ ብልጫ በማሳየት 22 ነጥብ 98 ቢሊየን ብር መድረሱን አንስተዋል። ከጠቅላላ ኢንቨስትመንቱ 20 ነጥብ 97 ቢሊየን ብር በመንግሥት ግምጃ ቤት ሰነድ ላይ ውሏል፤ ቀሪው 2 ነጥብ 01 ቢሊየን ብር ደግሞ በሙዳራባህ የቁጠባ ኢንቨስትመንት ሂሳብ መቀመጡን አስታውቀዋል። በ2018 በጀት ዓመት 9 ነጥብ 35 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ በታቀደው መሠረት፤ እስካለፈው ዘጠኝ ወር 6 ነጥብ 76 ቢሊየን ብር መሰብሰብ መቻሉን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ የተሰበሰበውን አርቦንም በአግባቡ ኢንቨስትመንት ላይ በማዋል የፋይናንስ ተቋማትን ጤናማነትና ተወዳዳሪነት የሚያጎለብት አቅም እየተገነባ መሆኑን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ተጠሪነቱን ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ በማድረግ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 482/2013 መቋቋሙ ይታወሳል። የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ ከብሔራዊ ባንክ፣ ከኢትዮጵያ ባንኮች ማኅበርና ከኢትዮጵያ የማይክሮ ፋይናንስ ማኅበር በተውጣጡ አምስት የዳይሬክተሮች ቦርድ የሚመራ ተቋም ነው።
በክልሉ የሌማት ትሩፋት ትግበራ የወተት ምርታማነት እንዲጨምር አስተዋጽኦ አበርክቷል - ቢሮው
Jun 16, 2026 273
ሆሳዕና፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የሌማት ትሩፋት የወተት ልማት ምርታማነት እንዲጨምር አስተዋጽኦ ማበርከቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የምግብ ሉአላዊነትን የማረጋገጥና ክብርን የማስጠበቅ ዓላማ ያለው ሲሆን በተለይ በወተት፣ ሥጋ፣ እንቁላልና ማር ትርፍ ምርት በማምረት መጠቀም ላይ ያተኮረ ነው። መርሀግብሩ የኢትዮጵያን ደካማ አምራችነት ታሪክ በመቀየር የምግብ ሉአላዊነትን ማረጋገጥና የኢኮኖሚ እድገትን የማፋጠን ግብም አለው። መርሃ ግብሩ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ተግባራዊ መደረግ ከጀመረ በኋላም የወተት ምርታማነትን በማሳደግ ዜጎችን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እያደረገና ገበያን ለማረጋጋት አቅም እየፈጠረ መጥቷል፡፡ በጉዳዩ ላይ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር እንደገለፁት፣ በክልሉ የሌማት ትሩፋት መርሀግብር የወተት ምርታማነት ለማሳደግ፣ የእንስሳት ዝርያን ለማሻሻል፣ የመኖ አቅርቦት እንዲጠናከር እንዲሁም በእንሰሳት ጤና አጠባበቅ ላይ ውጤት አምጥቷል። የወተት ምርታማነት ከማሳደግ ባለፈ የገበያ ትስስርና እሴት ጨምሮ ለገበያ ማቅረብ ላይ በመሰራቱ በክልሉ 12 የወተት ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪዎች እንዲቋቋሙ መደላድል መፈጠሩንም አቶ ኡስማን ጠቅሰዋል።   በሆሳዕና ከተማ በእንስሳት እርባታ ዘርፍ የተሰማሩት አቶ አዳነ አባቴ እንደገለፁት ወደዘርፉ ከገቡ ሰባት ዓመታትን ቢያስቆጥሩም በተሻለ ተጠቃሚ ሳይሆኑ ቆይተዋል። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ትግበራን ተከትሎ መንግስት በዘርፉ የተሰማሩ ዜጎች እንዲጠቀሙ የእንስሳት ዝርያ ማሻሻል ሥራ መስራቱ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል። በዚህም ዝርያቸው የተሻሻሉ ጥጆችን በማግኘት የወተት ምርታማነትን እያሳደጉ ከመምጣታቸው ባለፈ ገቢያቸውም እንዲጨምር ማድረጉን ገልጸዋል።   በሀድያ ዞን ሌሞ ወረዳ ሹርሞ ዊጥቢራ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ዘነበች ጋርከቦ በበኩላቸው እንዳሉት በሌማት ትሩፋት መረሀ ግብር ታቅፈው የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው ላሞችን በማርባት በወተት ልማት ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። መንግስት በፈጠረው ዕድል ተጠቅመው ከዚህ ቀደም የነበሯቸውን የወተት ላሞች ዝርያ በተሻሻሉ ዝርያዎች በመተካት ምርታማነታቸውን እያሳደጉ መሆኑን ገልጸዋል።      
በዞኑ የተገነቡ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ጥያቄዎቻችንን የመለሱ ናቸው - ነዋሪዎች
Jun 16, 2026 456
አምቦ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሸዋ ዞን የተገነቡ የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ለረጅም ጊዜ ሲያነሱት የነበረውን የልማት ጥያቄ እንደመለሰላቸው የዞኑ ነዋሪዎች ገለጹ። ምዕራብ ሸዋ ዞን ከፍተኛ የግብርና ምርትና የንግድ እንቅስቃሴ ያለበት ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፣ ቀደም ሲል የነበሩት የመሰረተ ልማት እጥረቶች ምርትን በወቅቱና በጥራት ወደ ገበያ ለማቅረብ እንዲሁም ነዋሪዎች ፈጣን ማህበራዊ አገልግሎቶችን ለማግኘት ምቹ ሁኔታ እንዳይፈጠር አድርገው ቆይተዋል። ይህንን ክፍተት ለመሙላት በፌደራል፣ በክልልና በዞኑ አስተዳደር የተቀናጀ ጥረት የተገነቡት የልማት ፕሮጀክቶች በአሁኑ ወቅት ተጠናቀው ለአገልግሎት ክፍት መሆናቸው በነዋሪዎች ህይወት ላይ አዎንታዊ ለውጥ በማምጣት ላይ ናቸው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የዞኑ ነዋሪዎች እንዳሉት በአሁኑ ወቅት ተጠናቀው ለአገልግሎት የበቁት የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች፣ ቀደም ሲል የነበሩትን ክፍተቶች በከፍተኛ ደረጃ በመፍታት የቆየ ጥያቄያቸውን እየመለሰላቸው ነው። ከነዋሪዎቹ መካከል የቶኬ ኩታዬ ወረዳ ነዋሪ የሆነው ወጣት ዳንኤል ባይሳ፤ በወረዳው የተከናወኑ የንጹህ መጠጥ ውሃና የመንገድ ግንባታ ስራዎች የአካባቢውን ማህበረሰብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ናቸው። በተለይም የመንገዱ መገንባት የሚያመርቱትን ምርት በቀላሉ ወደ ገበያ በማቅረብ ያጋጥም ለነበረው ችግር ዘላቂ መፍትሄ መስጠቱን ጠቁሟል። ፕሮጀክቶቹ በተለይም ለአካባቢው ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል መፍጠራቸውን ጠቅሶ፤ እሱም የዚህ እድል ተጠቃሚ መሆኑን ተናግሯል። የተገነቡ ልማቶችን ደህንነት በመጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ ከሌሎች ወጣቶች ጋር በቅንጅት እንደሚሰሩም ተናግሯል። ሌላኛዋ የአምቦ ወረዳ ነዋሪ ወይዘሮ ጋዲሴ ቡልቶ በበኩላቸው፤ ለብዙ ዓመታት በአካባቢያቸው የመንገድ መሰረተ ልማት ባለመኖሩ በኑሯቸው ላይ ከፍተኛ ችግር አድርሶባቸው እንደነበር አስታውሰዋል። አሁን ላይ ግን የመንገድ፣ የትምህርት ቤት እና የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው፤ የመሰረተ ልማት ዝርጋታው የቆየ ጥያቄያቸውን የመለሰና በተለይም ሴቶችን እኩል ተጠቃሚ ያደረገ በመሆኑ መደሰታቸውን ገልጸዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አበበ ጨመዳ፤ በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከ5 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ግንባታ ሲከናወን መቆየቱን ገልጸዋል። ከፕሮጀክቶቹ መካከል የመንገድ፣ የትምህርት፣ የጤና እና የንጹህ መጠጥ ውሃ ተቋማት ግንባታ በዋናነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ገልጸዋል። መንግስት በበጀት ዓመቱ የህዝብ ጥያቄ የነበሩ ፕሮጀክቶችን በተያዘላቸው ጊዜ፣ በጥራትና በብዛት አጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት እያደረገ መሆኑንም አክለዋል። በዞኑ በ2018 በጀት ዓመት የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ 675 የተለያዩ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶችን ለመስራት ታቅዶ፣ እስካሁን 519 የሚሆኑት ተገንብተዋል ብለዋል። ፕሮጀክቶቹ በተቀመጠላቸው ጊዜና ጥራት እንዲጠናቀቁ የዞኑ ህብረተሰብ ያበረከተው አስተዋጽኦ የጎላ መሆኑን የገለጹት ምክትል አስተዳዳሪው፤ ለአብነትም የባህላዊ ፍርድ ቤቶች፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ እና ሌሎች የልማት ስራዎች እንዲስፋፉ ህዝቡ ትልቅ እገዛ ማድረጉን ጠቅሰዋል። በበጀት ዓመቱ የታቀዱ የልማት ፕሮጀክቶች ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቁ የዞኑን ነዋሪዎች ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ መሆኑንና ለበርካታ ስራ አጥ ወጣቶችም የስራ እድል እንደሚፈጥሩ ገልጸዋል። እነዚህ በህዝብና በመንግስት ተሳትፎ የተገነቡ ፕሮጀክቶች በሁለት ዙር ተከፍለው የምርቃ መርሃ ግብር እየተካሄደ መሆኑን ገልጸው፤ በመጀመሪያው ዙር 391 ፕሮጀክቶች ተመርቀው ለአገልግሎት ክፍት ሆነዋል ብለዋል። በሁለተኛው ዙር ደግሞ ግንባታቸው ሙሉ በሙሉ የተጠናቀቀ 128 ፕሮጀክቶች በቅርቡ የምርቃ መርሃ ግብር እንደሚካሄድ ገልጸዋል።    
ኮርፖሬሽኑ በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው አብሮነትን መርኅ አድርጎ ነው - ረሻድ ከማል (ዶ/ር)
Jun 16, 2026 234
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፡-የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው የጋራ ተጠቃሚነትን፣ አብሮነትን እና ወንድማማችነትን መርኅ አድርጎ መሆኑን የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ኮርፖሬሽኑ የመኖሪያና የንግድ ቤቶችን ለመገንባት የሚያስችለውን ስምምነት ማድረጉን ተከትሎ፤ የደቡብ ሱዳን መንግሥት የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በጁባ ከተማ ለሚያከናውነው የዘመናዊ ቤቶች ግንባታ አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን አስታውቋል።   በዚህም መሠረት፤ የሕንጻ ግንባታ ሳይቶች መረጣ እና ተያያዥ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች አፈጻጸምም በግዛቱ የኮንስትራክሽን እና ቤቶች ኮርፖሬሽን በቀረበ የጥናት ሪፖርት አማካኝነት በዝርዝር ተገምግሟል። ቀደም ሲል በአዲስ አበባ የተፈረመውን የመግባቢያ ስምምነት ወደ ተግባር የሚያስገባው ይኸው አዲስ ውልም በጁባ ከተማ መፈረሙን ኮርፖሬሽኑ ለኢዜአ የላከው መረጃ አመላክቷል። ስምምነቱን የፈረሙትም፤የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) እና የደቡብ ሱዳን ሴንትራል ኢኳቶሪያል ግዛት አሥተዳዳሪ ኢማኑኤል አድል ናቸው። በዚህም መሠረት ኮርፖሬሽኑ በጁባ ከተማ ዘመናዊ የንግድና የመኖሪያ ሕንጻዎችን የሚገነባ ይሆናል።   ከዚሁ ጋር ተያይዞ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) ከደቡብ ሱዳን መንግሥት ልዩ መልዕክተኛ አዱት ኪር ጋር ውጤታማ ውይይት አድርገዋል። ዋና ሥራ አስፈጻሚው በዚሁ ወቅት፤ የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በደቡብ ሱዳን የቤት ልማት ዘርፍ የተሰማራው የጋራ ተጠቃሚነትን፣ አብሮነትን እና ወንድማማችነትን መርኅ አድርጎ መሆኑን አስገንዝበዋል። በአጭር ጊዜ ውስጥ ሙሉ በሙሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን አጠናቆ ግንባታውን በይፋ እንደሚጀምርም አረጋግጠዋል። አዱት ኪር በበኩላቸው፥ ኮርፖሬሽኑ በጁባ ከተማ ለሚያካሂደው የቤት ልማት ፕሮግራም የደቡብ ሱዳን የፌዴራል መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። ይህ የቤት ግንባታ መጀመር በሁለቱ እህትማማች ሀገራት መካከል ያለውን ጠንካራና ታሪካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው ያላቸውን ሙሉ እምነትም ገልጸዋል። የደቡብ ሱዳን መንግሥትም ለስምምነቱ ተግባራዊነት ያለውን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም