ቀጥታ፡
ኢኮኖሚ
በክልሉ አጠቃላይ በቡና ከሚለማው መሬት ውስጥ 20 በመቶውን በመስኖና በኩታ ገጠም ለማልማት ይሰራል
Jun 19, 2026 677
አዳማ፣ ሰኔ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል አጠቃላይ በቡና ከሚለማው መሬት ውስጥ 20 በመቶውን በመስኖና በኩታ ገጠም ለማልማት ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ የደረጃው የሚገኙ የቡና ልማት ባለሙያዎች፣ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት የቡና ምርታማነትን በማሳደግ ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ ተጠናቋል።   የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ በየደረጃው ያሉ ባለሙያዎች ሳይንሳዊ አሠራርንና ሙያን ብቻ መሠረት ባደረገ መልኩ የተቀናጀ ርብርብ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል። ለዚህም ሲባል አዲስ የቡና ልማት ፓኬጅ ተቀርዖ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው ፓኬጁ ከባለሀብቱና ከአርሶ አደሩ ማሳ እስከ ገበያ ያለውን የቡና እሴት ሰንሰለት የተከተሉ አዳዲስ አሠራሮችን ያካተተ መሆኑን ተናግረዋል። በዚሁ መነሻነት በክልሉ ከሚለማው አጠቃላይ የቡና መሬት ውስጥ 20 በመቶው በመስኖና በኩታ ገጠም እንደሚለማም ኃላፊው ገልጸዋል። ይህም በዓመት አንድ ጊዜ ብቻ የሚመረተውን የቡና ምርት ወደ ሁለት ጊዜ ለማሳደግ መታቀዱን አስረድተው በሄክታር የሚገኘውን ምርት ማሳደግ እንደሚገባም ገልጸዋል። በተለይም የቡና ልማትን በመስኖ ለማከናወን በውሃ አጠቃቀም ላይ ሙያዊና ሳይንሳዊ የቡና ልማት ሥነ-ዘዴን መከተልና መተግበር እንደሚገባ አሳስበዋል። የግብርና ምርምር ማዕከላት፣ በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች፣ የቡና ልማት ባለሙያዎችና የልማት ጣቢያ ሠራተኞች አርሶ አደሩን በንቃት ባሳተፈ መልኩ የቡና ምርታማነትን ለማሳደግ በቅንጅት መሥራት እንዳለባቸውም አሳስበዋል። ከአርሶ አደሩ ማሳ እስከ ግብይት ድረስ የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እንዲሁም ጥራቱን ለመጠበቅ የባለድርሻ አካላት ቅንጅታዊ ርብርብ ወሳኝ ነውም ብለዋል።   በማጠቃለያ መድረኩ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የቡና ልማት ምርታማነትን ለመጨመርና ጥራቱን የጠበቀ ምርት በብዛት ለዓለም ገበያ ለማቅረብ በትኩረት መሥራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ቀደም ሲል የቡና ልማት በባህላዊ መንገድና በዘልማድ የሚከናወን በመሆኑ ተገቢውን ትኩረት አላገኘም ያሉት ዳይሬክተሩ፤ ዘርፉ ላይ መሠረታዊ ለውጥ ለማምጣት ልዩ ትኩረት ይሰራልም ብለዋል።  
ረቂቅ አዋጁ ወጥ የሆነ ብሔራዊ ስታቲስቲክስ ሥርዓት በመፍጠር ጠንካራ የሕግ ማዕቀፍ መዘርጋት የሚያስችል ነው
Jun 19, 2026 484
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ወጥ የሆነ ብሔራዊ ስታቲስቲክስ ሥርዓት በመፍጠር ጠንካራ የሕግ ማዕቀፍ መዘርጋት የሚያስችል እንደሆነ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ ረቂቅ አዋጅ ቁጥር 23/2018 ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ይፋዊ የሕዝብ ውይይት መድረክ አካሂዷል።   የፕላንና ልማት ሚኒስቴር አማካሪ አቶ ቢራቱ ይገዙ የረቂቅ አዋጁን መነሻ ሐሳብ ባቀረቡበት ወቅት፤ አዋጁ የኢትዮጵያን ስታቲስቲክስ ሥርዓት ለማጠናከርና የበለጠ ለማዳበር፣ እንዲሁም ሥርዓቱን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍ ዘመኑን የዋጀ ለማድረግ የሚያስችል ነው ብለዋል። በዚህም የመረጃ ጥራትንና ተደራሽነትን በማሻሻል እንዲሁም ግልጽነትን በማረጋገጥ፣ መረጃው ተአማኒነት እንዲኖረው የሚያደርግ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም የሚቀርቡ መረጃዎች በዓለም አቀፍ ደረጃ ቅቡልነትን ማረጋገጥ በሚያስችል ሁኔታ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ በረከት ፍስሃጽዮን በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ ሁሉን አቀፍ የሆነ ብሔራዊ ስታቲስቲክስ ሥርዓት መፍጠር የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል።   በሥርዓቱ የሚሳተፉ አካላትን ሥልጣንና ኃላፊነት በግልጽ በመዘርዘር፣ የአገልግሎቱን የሙያ ነፃነት ይበልጥ በማጠናከር በስታቲስቲክስ ሥርዓቱ የምንከተላቸውን መርሆችና አሠራሮች በግልጽ የሚደነግግ መሆኑን ጠቁመዋል። እንዲሁም በስታቲስቲክስ ረገድ የመጡ አዳዲስ ለውጦችን ከቴክኖሎጂም ከሥነ-ዘዴዎችም አኳያ በአግባቡ ያስቀመጠ መሆኑን ጠቁመው፤ መንግሥት በመረጃ ላይ የተመሠረተ ፖሊሲ እንዲያወጣና ውሳኔ እንዲሰጥ የሚያግዝ መሆኑን አስገንዝበዋል። በመድረኩ የተገኙ የተለያዩ የማኅበረሰብ አካላት በበኩላቸው፤ ለረቂቅ አዋጁ ግብዓት የሚሆኑ ሐሳቦችንና አስተያየቶችን ሰጥተዋል። ረቂቅ አዋጁ የሙያ ነፃነት በመስጠት ከፍተኛ መጠን ያላቸውን መረጃዎች ለመተንተን ቴክኖሎጂ እና ሰው ሠራሽ አስተውሎት መጠቀምን የሚያበረታታ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም ብሔራዊ የስታቲስቲክስ ሥርዓት ለመዘርጋት ያለመ በመሆኑ አስፈላጊና ወቅቱን የጠበቀ መሆኑን ጠቅሰው፤ ነገር ግን ብሔራዊ ሥርዓት ሲዘረጋ የክልሎች ሥልጣን አይጋፋም ወይ? እንዴትስ ለማጣጣም ታስቧል? የሚሉ ጥያቄዎችን አንስተዋል።   የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር በከር ሻሌ (ዶ/ር) በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ፤ ክልሎች የራሳቸው የስታቲስቲክስ አዋጅ ቢኖራቸውም፣ የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ሲባል ከፌዴራል መንግሥት ጋር በቅንጅት የሚሠሯቸው ሥራዎች መኖራቸውን ገልጸዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች የተነሱ ጠቃሚ ሐሳቦችና አስተያየቶችም አዋጁ ሲወጣ በግብዓትነት እንደሚወሰዱ ተናግረዋል።   በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጆ በበኩላቸው፤ ረቂቅ አዋጁ ወጥ የሆነ ብሔራዊ ስታቲስቲክስ ሥርዓት በመፍጠር ሥርዓቱን መምራት የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍ ለመዘርጋት የሚረዳ ነው ብለዋል። ለዚህም ቋሚ ኮሚቴው አዋጁ ጠንካራና ታማኝ የመረጃ ሥርዓት መዘርጋት በሚያስችል መልኩ ጸድቆ እንዲወጣ እንደሚሠራ ገልጸዋል።    
በክልሉ የግብርና ግብአትና የማሽነሪ አቅርቦትን በማሳለጥ ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው
Jun 19, 2026 234
ወላይታ ሶዶ፣ ሰኔ 12/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና ግብአትና የማሸነሪ አቅርቦትን በማሳለጥ የግብርና ልማትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑ ተገለጸ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሁለገብ ሕብረት ሥራ ማህበራት ፌደሬሽን ምስረታ ጉባኤ ዛሬ በወላይታ ሶዶ ከተማ ተካሂዷል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) የሕብረት ሥራ ማህበራትን አቅም በማደራጀት የክልሉን አርሶ አደሮችንና አርብቶ አደሮችን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለማድረግ በተሰራው ሥራ ውጤት እየተመዘገበ ነው። የግብርና ግብአትና የማሸነሪ አቅርቦትን በማሳለጥ የግብርና ልማትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑም ተናግረዋል። ይህን ለማጠናከር ፌደሬሽን ማቋቋም አስፈላጊ እንደሆነ ጠቁመው፣ የፌደሬሽኑ መቋቋም የአርሶ አደሩን እንዲሁም የአርብቶ እና ከፊል አርብቶ አደሮችን ኢኮኖሚ ለማሳደግ የጎላ ድርሻ አለው ብለዋል። የግብርና ምርትን ከማሳ እስከ ተጠቃሚዎች ለማድረስ እንዲሁም የሜካናይዜሽን ማሽነሪዎችን ጨምሮ ሌሎች የግብርና ግብአቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ የፌደሬሽኑ መቋቋም ጠቀሜታው የጎላ ነው ሲሉም አክለዋል። የክልሉ መንግስት የግብርናውን ዘርፍ ይበልጥ ለማነቃቃት እንዲሁም የዘርፉን ተዋንያን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በልዩ ትኩረት ይደግፋል ሲሉም መሪሁን (ዶ/ር) አረጋግጠዋል። በክልሉ 6 ሺህ 381 መሰረታዊ እና 30 የሕብረት ሥራ ዩኒየኖች እንዳሉ የተናገሩት ደግሞ የክልሉ ሕብረት ሥራ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳሙኤል ፎላ ናቸው።   እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ፣ የሕብረት ሥራ ማህበራት በኢኮኖሚ ውስጥ የሚጠበቅባቸውን ሚና በአግባቡ እንዲወጡና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የተቀረጸው የማሻሻያ ሪፎርም ውጤት እያስገኘ ነው። የህብረት ሥራ የሪፎርም ትግበራ ከተጀመረ ወዲህ ዜጎች በህብረት ስራ የመደራጀት፣ የቁጠባ፣ የብድር ስርጭት መጠንና አመላለስ እንዲሁም የሀገር ውስጥና የውጭ ግብይት መጠን እያደገ መጥቷል ብለዋል። በክልሉ 17 የሕብረት ሥራ ማህበራትን በማቀፍ የተመሰረቱ ዩኒየኖችን አቅም በማቀናጀት በሁለገብ ህብረት ሥራ ፌደሬሽን እንዲደራጁ መደረጉንም ጠቁመዋል። ዛሬ በክልሉ ለመጀመሪያ ጊዜ የተመሰረተው ፌደሬሽን የግብርና ግብአቶችንና ማሽነሪዎችን በማቅረብና ሜካናይዜሽን እርሻን በማስፋፋት በግብርና ልማት አርሶ አደሩን ያግዛል ብለዋል።   የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ በበኩላቸው በሕብረት ስንቆም አቅማችንን አደራጅተን ለሀገር ዕድገትና ልማት የተሻለ ነገር መፍጠር እንችላለን ብለዋል። በመሆኑም የዞኑን አርሶ አደሮች ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በዘርፉ የተቋቋሙ ማህበራትን አቅም የማጎልበት ሥራ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በመድረኩ የክልልና የዞን ሥራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት የተገኙ ሲሆን በወላይታ ሶዶ ከተማ የገንዘብ ብድርና ቁጠባ ሕብረት ሥራ ማህበራት የሥራ እንቅስቃሴም ተጎብኝቷል።
ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራን በማጠናከር የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jun 19, 2026 356
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 12/2018(ኢዜአ)፦ ክህሎት መር የሥራ ዕድል ፈጠራን በማጠናከር የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ገለጹ፡፡ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በለውጡ መንግሥት የተተገበሩ የሪፎርም ሥራዎች የወጣቶችን ኢኮኖሚና ማኅበራዊ ተጠቃሚነት የሚያጎለብቱ ተጨባጭ ውጤቶችን አስገኝተዋል።   ባለፉት 4 ዓመታት በተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ የሪፎርም ሥራዎች ለ19 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቁመው፣ ከዚህም መካከል 75 በመቶ በላይ የሚሆኑት ወጣቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። ለውጡ ካስገኛቸው ዋና ዋና ስኬቶች መካከል ወጣቶች ከተለመደው የቅጥር ሐሳብ ወጥተው ወደ ሥራ ፈጣሪነት እንዲሸጋገሩና ለሌሎች የሥራ ዕድል እንዲፈጥሩ ምቹ ሁኔታዎችን መፈጠራቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡   በተጨማሪም የቤተሰብ የንግድ ሥራዎች እንዲስፋፉ በማድረግ ረገድ አበረታች ውጤቶች መገኘታቸውን አክለዋል፡፡ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎች መስፋፋትና ለዘርፉ የተሰጠው ልዩ ትኩረት ለወጣቶች ዘመናዊ፣ ፈጣንና ምቹ የሥራ ዕድሎችን የፈጠረ ሲሆን፣ ይህም በዓለም አቀፍና በአህጉራዊ የዲጂታል የሥራ ገበያ ላይ የሀገሪቱንና የወጣቶቹን ተወዳዳሪነት ማሳደጉን አብራርተዋል።   የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሙና አሕመድ በበኩላቸው፤ ከለውጡ በኋላ የወጣቶችን አቅም በማሳደግ ረገድ ሰፊ ስራዎች መሰራታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም ተስፋ ሰጪ፣ ዘላቂና ክህሎት መር የሥራ ዕድሎችን በተሻለ ሁኔታ ለመፍጠር ትልቅ አቅም መገንባቱን አብራርተዋል። በመዲናዋ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ ከሆኑት መካከል ወጣት ጋሻው ዓለሙ የመኪና ጎማና ባትሪዎችን መልሶ ጥቅም ላይ የማዋል ሥራ ላይ መሰማራቱን ጠቅሷል፡፡ የምናመርታቸው ምርቶች የአካባቢ ብክለትን ከመቀነስና ቆሻሻን ወደ ሀብት ከመቀየር ባለፈ፣ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን የሚያሳድጉና ሰፊ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ ናቸው ብሏል። በማኅበር በመደራጀት ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን የሚተኩ የቤትና የቢሮ መገልገያ ቁሳቁሶችን እያመረቱ መሆናቸውን የተናገረው ደግሞ ወጣት አስቻለው ጌትዬ ነው፡፡ በቀጣይም የምርቶቻቸውን የገበያ ተደራሽነትና የሥራ ዕድሎችን ይበልጥ ለማስፋፋት እየሠሩ መሆናቸውን ተናግሯል።
በክልሉ በማዕድን ዘርፍ ለሚሰማሩ ባለሃብቶች አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል -ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ
Jun 19, 2026 175
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በሀረሪ ክልል በማዕድን ዘርፍ ለሚሰማሩ ባለሃብቶች አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩና ካቢኔያቸው በክልሉ በማዕድን ዘርፍ እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።   አቶ ኦርዲን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በክልሉ በዘርፉ በተለይም በግራናይትና ላይምስቶን ምርት ያለውን እምቅ ሃብት ጥቅም ላይ በማዋል ረገድ አበረታች ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። እየተከናወኑ በሚገኙ ስራዎችም በርካታ ዜጎች የስራ እድል ተጠቃሚ መሆናቸውን አመልክተዋል። በዘርፉ ያለውን ሃብት በአግባቡ መጠቀም ያለው ፋይዳ ከፍተኛ መሆኑን ገልጸው፤ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉም በትኩረት ይሰራል ብለዋል።   በክልሉ በማዕድን ዘርፍ የተሰማሩ አልሚዎችን ከማበረታታት ባሻገር፤ አዳዲስ በዘርፉ ለሚሰማሩ ባለሃብቶች አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግም ነው ርዕሰ መስተዳድሩ የተናገሩት።
የቡናን ጣዕም የሚያስጠብቁ ቴክኖሎጂዎችን በማስፋት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የሚከናወኑ ተግባራት ይጠናከራሉ
Jun 19, 2026 220
ሃዋሳ፤ ሰኔ 12/2018 (ኢዜአ)፦የቡናን ተፈጥሯዊ ጣዕም የሚያስጠብቁ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማስፋት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን አስታወቀ፡፡ በሲዳማ ክልል ቨርሚ ኮምፖስት በዘመናዊ መንገድ አዘጋጅቶ መጠቀም ላይ ለልምድ ልውውጥ የተዘጋጀ መድረክና የመስክ ጉብኝት ተካሂዷል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ አዳዲስ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት የቡናን ተፈጥሯዊ ጣዕም ለማስጠበቅ እየተሰራ ነው። ባለስልጣኑ በቡና ግብይትና ልማት ላይ አዳዲስ የሪፎርም ሥራዎችን መጀመሩ የቡና ምርታማነትና ጥራትን በማስጠበቅ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተፈላጊ የሆነውን የኢትዮጵያን ቡና ተፈጥሯዊ ጣዕም የሚያስጠብቁ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የተጀመሩ ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። ለእዚህም በክልሎች ያለውን ተሞክሮ የመቀመር ሥራ በትኩረት እንደሚከናወን ነው የገለጹት። በተለይ በሲዳማ ክልል ቡና የሚያዘጋጁ ኢንዱስትሪዎችን ከአርሶ አደሮች ጋር በማስተሳሰር የተጀመረው የቨርሚ ኮምፖስት አጠቃቀም የቡናን ጥራት ለማስጠበቅ የጎላ ድርሻ ስላለው በሌሎች ክልሎችም ይጠናከራል ብለዋል፡፡ የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተርና የልማት ዘርፍ ሃላፊ አቶ ታጋይ ኑሩ በበኩላቸው እንዳሉት፤ የቡናን ጥራትና ምርታማነት ለማስጠበቅ የተቀረጹ ፓኬጆችን ተግባራዊ በማድረግ ተፈጥሯዊ ጣዕሙን የጠበቀ ቡና እየተመረተ ነው። ለዚህም የተፈጥሮ ማዳበሪያ አጠቃቀምን የማጠናከር ሥራ ትኩረት እንደተሰጠው ገልጸው፣ ቨርሚ ኮምፖስት በሲዳማ ክልል ተሞክሮ ውጤታማ የሆነ አዲስ ቴክኖሎጂ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ቨርሚ ኮምፖስትን ጨምሮ የተፈጥሮ ማዳበሪያ በእያንዳንዱ አርሶ አደር ማሳ በማዘጋጀት ዓለም አቀፍ እውቅና የተሰጠውንና ተፈጥሯዊ ይዘቱን የጠበቀ ቡና የማቅረብ ተግባር ይጠናከራል ብለዋል፡፡ በክልሉ በቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎች እና በሞዴል አርሶ አደሮች ማሳ የተጀመረው የቨርሚ ኮምፖስት ዝግጅትና አጠቃቀም የቡና ጥራትና ምርታማነትን አሳድጓል ያሉት ድግሞ የሲዳማ ክልል ቡና፣ ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መስፍን ቃሬ ናቸው፡፡ የቡና ጥራትና ምርታማነትን ለማሳደግ የተቀረጹ 12 ፓኬጆች እንዳሉ ጠቅሰው፣ የተፈጥሮ ማዳበሪያ አጠቃቀም ቀዳሚ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት ጥቅም ላይ የዋላው የቨርሚ ኮምፖስት በ45 ቀናት ውስጥ ተዘጋጅቶ የሚደርስ፣ ጊዜን እና ጉልበትን የሚቆጥብ ነው ብለዋል፡፡ በጉብኝቱ ላይ ከተሳተፉት መካከል የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡናና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ አማኑኤል ብሩ፣ በሲዳማ ክልል ቨርሚ ኮምፖስት በዘመናዊ መንገድ የማዘጋጀት ሥራ ልምድ ያገኙበት መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ የቡና ኢንዱስትሪዎችን ከአርሶ አደሩ ጋር የማስተሳሰር ተሞክሮው መስፋት ስላለበት በክልላቸው እንደሚተገበር ተናግረዋል፡፡ በዳሌ ወረዳ ሾኢ ቀበሌ በቨርሚ ኮምፖስት አዘገጃጀት ተሞክሯቸውን ያካፈሉት የተደራጁ ወጣቶች በበኩላቸው እንዳሉት፤ ኮምፖስቱን ለገበያ በማቅረብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እያሳደጉ መጥተዋል። ባለስልጣኑ በሲዳማ ክልል በአርሶ አደሮችና በቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎች ያለውን የቨርሚ ኮምፖስት አዘገጃጀት ልምድ ለመለዋወጥ ባዘጋጀው ጉብኝት ላይ ከ5 ቡና አብቃይ ክልሎች የመጡ አርሶ አደሮችና የሚመለከታቸው አካላት ተሳትፈዋል፡፡
በዞኑ ዘመናዊ የመሬት አስተዳደር ስርዓትን በማስፈን የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው
Jun 19, 2026 157
ደብረ ማርቆስ ፤ ሰኔ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዘመናዊ የመሬት አስተዳደር ስርዓትን በማስፈን የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ መሬት መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ፈንታሁን ብርሃን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ዘመናዊ የመሬት አስተዳደር ስርዓትን በማስፈን የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ርብርብ እየተደረገ ነው።   በዚህም ባለፉት ዓመታት ለሁሉም አርሶ አደሮች ጊዜያዊ የመሬት ባለቤትነት ማስረጃ የመስጠት ሁኔታ እንደነበር ገልጸው ዘንድሮ ይህንን ወደ ቋሚ ይዞታ ማረጋገጫ በማሳደግ የባለቤትነት መብታቸውን ለማረጋገጥ በትኩረት መሰራቱን ገልጸዋል። እስካሁን በተደረገው ጥረትም ከ600 ሺህ በላይ ለሚሆኑ አርሶ አደሮች በካርታ የተደገፈ ቋሚ የመሬት ባለቤትነት ማረጋገጫ ደብተር በማሰራት ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። ቋሚ የመሬት ማረጋገጫ ካገኙት አርሶ አደሮች ከ3 ሺህ 586 በላይ ለሚሆኑት ከ130 ሚሊዮን ብር በላይ የባንክ ብድር አግኝተው በሌሎች የገቢ ማስገኛ ዘርፎች ለመሰማራት እድል እንደተፈጠረላቸው አብራርተዋል። በተጨማሪም ዋስትና በማግኘታቸው የእርሻ ማሳቸውን ለምነት በመጨመር ዘላቂ ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ያለፈ ምርት ለማምረት መነሳሳትን ፈጥሮላቸዋል። ከሁለት ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ቀሪ አርሶ አደሮችን በካርታ የተደገፈ ቋሚ የይዞታ ማረጋገጫ ደብተር ተጠቃሚ ለማድረግም በየደረጃው ያለው አመራርና ባለሙያ ርብርብ እያደረገ እንደሚገኝም ገልጸዋል።   በዞኑ የእናርጅ እናውጋ ወረዳ የፈለገ ብርሃን ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ማማሩ ወርቅነህ እንደገለጹት፤ ቋሚ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ ደብተር ማግኘታቸው ከወሰን ማስከበር ጋር የነበረባቸውን ችግር እንዳስቀረላቸው ተናግረዋል። የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ደረጀ አጥናፉ በበኩላቸው፤ ቋሚ የመሬት ይዞታ ማረጋገጫ በማሰራታቸው በመሬታቸው ላይ ሙሉ የባለቤትነት ስሜት እንዲያዳብሩ እንዳደረጋቸው አስረድተዋል። በቀጣይም ደብተሩን አስይዘው በመበደር ከሰብል ልማት በተጨማሪ በሌሎች የገቢ ማስገኛ ስራዎች ላይ ለመሰማራት አቅደው እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በበጀት ዓመቱ ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የጠጠር መንገዶችና ድልድዮች ለአገልግሎት በቅተዋል
Jun 19, 2026 151
ደብረ ማርቆስ ፤ ሰኔ 12/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ምስራቅ ጎጃም ዞን በበጀት ዓመቱ ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተገነቡ የጠጠር መንገዶችና ድልድዮች ለአገልግሎት መብቃታቸውን የዞኑ መንገድ፣ ትራንስፖርትና ሎጅስቲክ መምሪያ አስታወቀ። የምስራቅ ጎጃም ዞን በግብርና ምርታማነትና በከብት እርባታ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ካላቸው የአማራ ክልል አካባቢዎች አንዱ ነው። ይሁን እንጂ በተለይም በክረምት ወቅት የሚስተዋለው የጭቃና የመንገድ መበላሸት ችግር፣ አርሶ አደሩ ምርቱን በወቅቱ ወደ ገበያ እንዳያቀርብ ትልቅ ማነቆ ሆኖ ቆይቷል። በክልሉ መንግስትና የዞኑ አስተዳደር ይህንን የመሰረተ-ልማት ክፍተት ለመሙላትና የገጠር-ከተማ ትስስርን ለማጠናከር በበጀት ዓመቱ ከ300 ሚሊዮን ብር በላይ የወጣባቸው የጠጠር መንገዶች ተገንብተዋል፡፡ የዞኑ መንገድ፣ ትራንስፖርትና ሎጂስቲክ መምሪያ ሃላፊ አቶ ማናየ አዳነ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የመንገድ መሰረተ ልማት ግንባታው የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መስተጋብር እያሳደገው ይገኛል።   ከመንግስትና ከማህበረሰቡ በተገኘ 300 ሚሊዮን ብር ወጪ የጠጠር መንገዶች መገንባታቸውን ጠቁመው፤ ከዚህም ውስጥ ከ72 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመተው ከማህበረሰቡ የተገኘ ነው ብለዋል። በዚህም 60 ኪሎ ሜትር አዲስ የጠጠር መንገድ ግንባታ፣ ከአንድ ሺህ ኪሎ ሜትር በላይ ነባር መንገድ ጥገናና ሶስት ተጠልጣይ ድልድዮች እንዲሁም የኮንክሪት ድልድይ መገንባት መቻሉን ተናግረዋል። ለመንገድ ግንባታና ጥገናውም ማህበረሰቡ በገንዘብ፣ በጉልበቱና በቁሳቁስ የላቀ አስተዋጽኦ በማበርከቱ የተሳካ ስራ እንዲሰራ ማስቻሉን አንስተዋል። በጎዛምን፣ አዋበል፣ እናርጅ፣ የጁቤ፣ ደብረ ኤልያስን ጨምሮ በስምንት ወረዳዎች የተከናወነው የመንገድና ድልድይ ግንባታ 325 የገጠር ቀበሌዎችን እርስ በእርስ ለማገናኘት ያስችላል ብለዋል። የመንገድና ድልድይ ግንባታው የዞኑ ህዝብ እስካሁን በእንስሳትና በሸክም ሲያጓጉዝ የነበረውን ሸቀጥና የግብርና ግብአት በመኪና በማጓጓዝ ፈጥኖ ለልማት ስራው እንዲደርስ የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። በዞኑ ጎዛምን ወረዳ የለቅለቂታ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ይግዛው አየለ እንደገለጹት፤ በበጀት ዓመቱ የተገነባላቸው የጠጠር መንገድ የግብርና ምርታቸውን ወደ ገበያ ለማቅረብና የግብርና ግብዓትን ለማጓጓዝ አስችሏቸዋል።
በፌዴራል ዋና ኦዲተር የኦዲት ሽፋን፣ ጥራትና ተደራሽነትን ለማሳደግ እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎች የሚበረታቱ ናቸው 
Jun 18, 2026 558
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 11/2018 (ኢዜአ):- የፌዴራል ዋና ኦዲተር የኦዲት ሽፋንን ጥራትና ተደራሽነት ለማሳደግ እየተከናወኑ የሚገኙ ስራዎች የሚበረታቱ መሆናቸውን የሕዝብ ተወካዮች የምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ ገለጹ። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን በ26ኛ መደበኛ ስብሰባው፤ የፌዴራል ዋና ኦዲተር ያቀረበውን የፌዴራል መንግሥት መሥሪያ ቤቶች የ2017 በጀት ዓመት የፋይናንሺያል፣ የሕጋዊነት እና የክዋኔ ኦዲት ሪፖርት ላይ ተወያይቷል። የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ ሪፖርቱን ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። ዋና ኦዲተሯ በሪፖርታቸው፤ በተቋማት በጀት አጠቃቀም፣ በተሰብሳቢ ሒሳብ መጠን እንዲሁም በፕሮጀክቶች ውል መቋረጥ ላይ መሻሻሎች መታየታቸውን አንስተዋል።   የምክር ቤቱ አባላት በበኩላቸው፤ የፌዴራል ዋና ኦዲተር የኦዲት ሽፋን ጥራትና ተደራሽነትን ለማሳደግ እያከናወናቸው የሚገኙት ሥራዎች የሚበረታቱ መሆናቸውን ገልጸዋል። በየዓመቱ የሚቋረጡ ፕሮጀክቶች ቁጥር እያነሰ መምጣቱን ሪፖርቱ የሚያመላክት መሆኑን ያነሱት የምክር ቤት አባላቱ፤ የኦዲት ጥራትንና ግልጽነትን ለማጠናከር በፌዴራል ዋና ኦዲተር በኩል እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎችንም አድንቀዋል። የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ በበኩላቸው፤ የኦዲት ጥራትን ለማሻሻል በርካታ ሥራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል። ከዚሁ ጋር ተያይዞም የተቋማትን የውስጥ ኦዲት ጥራት የሚያሻሽሉ የአቅም ግንባታ ሥራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑን ዋና ኦዲተሯ አስረድተዋል። የመንግሥት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሺእመቤት ደምሴ (ዶ/ር)፤ በ2017 በጀት ዓመት ለልማት ሥራዎች ከተመደበው በጀት ውስጥ የዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የ99 ነጥብ 3 በመቶ የኦዲት ሽፋን ማሳካት መቻሉን አስታውቀዋል።   በተጨማሪም የክዋኔ ኦዲት ትግበራ በየዓመቱ እያደገ መምጣቱ የተቋሙን የኦዲት አቅም ውጤታማነት እንደሚያሳይ ገልጸዋል። የቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዋ አክለውም፤ በየበጀት ዓመቱ በምክር ቤቱ የሚጸድቀው የኦዲት ሽፋን ሙሉ በሙሉ እንዲካሄድና ለክዋኔ ኦዲትም በቂ ሽፋን እንዲኖር ሁሉም ባለድርሻ አካላት ርብርብ ማድረግ ይገባቸዋል ብለዋል። የምክር ቤቱ ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ፤ የፌዴራል ዋና ኦዲተር ተወዳዳሪና ጠንካራ አሠራርን ለማጎልበት እያከናወናቸው የሚገኙት ተግባራት የሚበረታቱ መሆናቸውን ገልጸዋል። ምክትል አፈ ጉባኤዋ በየዓመቱ እየተገኙ ያሉ ለውጦችን ይበልጥ በማሳደግ እንዲሁም የታዩ ውስንነቶችን በዘላቂነት ለመፍታት የቅንጅት ሥራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ አሳስበዋል።
ከጎሮ እስከ ኮዬ ፈጬ አደባባይ ያለው አዲስ የኮሪደር ልማት ስራ ተጀመረ
Jun 18, 2026 480
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 11/2018 (ኢዜአ):- የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከጎሮ እስከ ኮዬ ፈጬ አደባባይ ድረስ ያለውን አዲስ የኮሪደር ልማት ስራ በተቀናጀና በተደራጀ አግባብ መጀመሩን አስታወቁ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ በመልእክታቸው፤ ከጎሮ መታጠፊያ እስከ ኮዬ ፈጬ አደባባይ ያስጀመርነው የኮሪደር ልማት አጠቃላይ የመንገዱ ርዝመት 10 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር ሲሆን፣ የመንገዱ ስፋት 70 ሜትር (ስምንት ሌን ያለው) ሆኖ ከነግሪነሪው 124 ሜትር ስፋት እንደሚኖረው ገልጸዋል።   ከዚህም በተጨማሪ 21 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የሳይክል መንገድ፣ 21 ኪሎ ሜትር ርዝመት እና በሁለቱም በኩል 4.5 ሜትር ስፋት ያለው የእግረኛ መንገድ፣ ሰፊ የአረንጓዴ ሽፋን እንዲሁም የፍሳሽ ማጣሪያ ጣቢያ በውስጡ እንደሚኖረው አመልክተዋል። ይህ የኮሪደር ልማት በከተማዋ ቀደም ሲል የለሙ መሰረተ ልማቶችን በከፍተኛ ሁኔታ የሚያስተሳስር፣ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴውን የሚያነቃቃ እና በመንገዱ ላይ ያለውን የትራፊክ መጨናነቅ የሚፈታ መሆኑን አመልክተዋል። መነሻውን ከቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ጋር ያደረገ በመሆኑም ሀገራዊ ሁነቶችን ለማስተናገድ አመቺ ሁኔታን እንደሚፈጥርና የአካባቢውን ስታንዳርድ በእጅጉ በሚያሳድግ ሁኔታ እንደሚሰራም ነው ያብራሩት።   በኮሪደሩ ላይ ሞሎች፣ የቢዝነስ ተቋማት እና ሌሎች ኮሚኒቲዎች እንደሚገነቡ ገልጸው ከዚህ ቀደም በመንገዱ ዙሪያ ከደረጃ በታች ይሰጡ የነበሩ አገልግሎቶችን ከፍ ባለ ደረጃ ለመስጠት በሚያስችል መልኩ በጥራትና በፍጥነት ለማጠናቀቅ በትልቅ ርብርብ እንደሚሰራም ከንቲባዋ ጠቁመዋል። ይህ ኮሪደር ከከተመዋ አልፎ ሀገራዊ ፋይዳ ያለው፣ ለአካባቢው ነዋሪ ሰፊ የስራ እድል የሚፈጥር፣ አካባቢውን ወደ ትልቅ የንግድ እንቅስቃሴ የሚቀይር ነው ብለዋል። በአካባቢው ላይ የሚኖሩ የከተማዋ ነዋሪዎች ትብብራቸው እንደ ወትሮው የተጠናከረ እንዲሆንና አብረን እንድንሰራ፤ እንዲሁም በስራው ውስጥ የሚሳተፉ ኮንትራክተሮች፣ ማህበራት፣ አማካሪዎች በአጠቃላይ ባለድርሻ አካላት በትብብር በፍጥነት በጋራ እንዲሳካ ከንቲባዋ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ለቤቶች ልማት የአገር ውስጥ የፋይናንስ አቅምን በውጤታማነት ለመጠቀም እየሰራ ነው
Jun 18, 2026 289
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 11/2018 (ኢዜአ):- የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ለቤቶች ልማት ፕሮጀክቶች የአገር ውስጥ የፋይናንስ አቅምን በውጤታማነት ለመጠቀም እየሰራ እንደሚገኝ የተቋሙ ዋና ስራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) ገለጹ። የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን እና የኦሮሚያ ባንክ የስትራቴጂካዊ አጋርነት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱን የተፈራረሙት የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር) እና የኦሮሚያ ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ተፈሪ መኮንን ናቸው።   ኮርፖሬሽኑ ለሚያከናውናቸው የቤት ልማትና ተያያዥ ሥራዎች አስተማማኝ የፋይናንስ ስትራቴጂካዊ አጋርነትን በማረጋገጥ ረገድ ስምምነቱ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወት ተመላክቷል። የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ረሻድ ከማል (ዶ/ር)፤ ኮርፖሬሽኑ ለሚያከናውነው ሰፊ የቤት ልማት ፕሮግራም የአገር ውስጥ የፋይናንስ አቅምን በውጤታማነት ለመጠቀም በትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል። የኦሮሚያ ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ተፈሪ መኮንን በበኩላቸው፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ስሙ በለውጥና በስኬት ከሚነሳው የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ጋር በትብብር መሥራት ለአገር ኢኮኖሚ ትልቅ ጠቀሜታ እንዳለው ተናግረዋል። ሁለቱ ወገኖች ለስምምነቱ ተፈጻሚነት ያላቸውን ከፍተኛ ቁርጠኝነት መግለጻቸውን የኮርፖሬሽኑ መረጃ ያመለክታል።
በምስራቅ ወለጋ ዞን ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም በኢንቨስትመንት ዘርፉ ተጠቃሚ ለመሆን እየሰራን ነው-ባለሀብቶች 
Jun 18, 2026 261
ነቀምቴ፤ ሰኔ 11/2018(ኢዜአ)፦ በምስራቅ ወለጋ ዞን ለኢንቨስትመንት ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ውጤታማ ለመሆን እየሰሩ መሆናቸውን በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ ባለሀብቶች ገለጹ። በዞኑ ሊሙ ወረዳ በግብርናው ዘርፍ በበቆሎ ምርት ላይ የተሰማሩት ባለሀብት አቶ አበራ ጎሹ እንደገለጹት፤ በአካባቢው ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም የግብርና ምርትና ምርታማነትን እያሳደጉ ይገኛሉ። በዚህም ከራሳቸው አልፈው ለሌሎች ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር መቻላቸውን ተናግረው በ8 ሚሊዮን ብር መነሻ ካፒታል በ100 ሄክታር መሬት ላይ በቆሎ እያመረቱ መሆኑን ገልጸዋል። የግብርና ሥራውን በማዘመን ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ መሆኑንና ይህም ለአካባቢው አርሶ አደሮች ጥሩ አርዓያ እየሆነ መምጣቱን ጠቁመዋል። በእርሻ ስራውም ለ9 ሰዎች ቋሚ፣ እንዲሁም በምርት ወቅት ከ50 እስከ 60 ለሚደርሱ ነዋሪዎች ጊዜያዊ የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን አስረድተዋል። ሌላኛው ባለሀብት አቶ ረጋሳ ኤጄታ በበኩላቸው፣ በሲቡ ስሬ ወረዳ ለሊሳ ቀበሌ በግብርና ሥራ ላይ መሰማራታቸውን ገልጸዋል። መንግስት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ዜጎች በተሰማሩበት ዘርፍ ውጤታማ እንዲሆኑ እያደረገ ያለውን ድጋፍና ምቹ ሁኔታ በመጠቀም እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ባለሀብቱ በቆሎ፣ ሩዝ፣ ኑግ እና አኩሪ አተር የተሻለ ምርት የሚገኝባቸው ሰብሎች መሆናቸውን ገልጸው በምርት ወቅት ከ100 እስከ 150 ለሚደርሱ የአካባቢው ነዋሪዎችን የሥራ ዕድል ተጠቃሚ እያደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል።   የምስራቅ ወለጋ ዞን ኢንቨስትመንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አለማየሁ ተስፋ፤ በዞኑ ሰፊ የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ መኖሩን ገልጸው፤ ባለሀብቶች በተለይም በማኑፋክቸሪንግ፣ በማዕድን እና በግብርና ዘርፎች ላይ በስፋት መሰማራታቸውን ተናግረዋል። በዞኑ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች 1 ሺህ 392 ባለሀብቶች በሥራ ላይ መሆናቸውን ገልጸው እነዚህ ባለሀብቶች በ2 ቢሊዮን ብር ካፒታል እየተንቀሳቀሱ ነው ብለዋል። በዞኑ በተመቻቸው የኢንቨስትመንት ዕድል 66 ሺህ ሄክታር መሬት ለባለሀብቶች የተሰጠ ሲሆን እስካሁን ከ26 ሺህ በላይ ወጣቶች የሥራ ዕድል ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን ተናግረዋል። ዞኑ በተለይ ለግብርና ሥራዎች ተመራጭ መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊው፤ በቆሎ፣ የቅባት እህሎች፣ የጥራጥሬ ሰብሎች፣ ቡና እና ሌሎች የአገዳ እህሎች በስፋት የሚመረቱበት አካባቢ መሆኑን ገልጸዋል። በመሰረተ ልማት አቅርቦት ረገድ ያሉ ጥያቄዎችንም ደረጃ በደረጃ ለመቅረፍ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም አስታውቀዋል።
በዞኑ የገቢ ምንጭን ለማስፋት እና ግንዛቤን ለማሳደግ በተሰራው ስራ ከዕቅድ በላይ ገቢ መሰብሰብ ተችሏል
Jun 18, 2026 147
ጅማ ፤ ሰኔ 11/2018(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ጅማ ዞን የገቢ ምንጭን ለማስፋት እና ግንዛቤን ለማሳደግ በተሰራው ስራ በዘንድሮው ዓመት ከዕቅድ በላይ ገቢ መሰብሰብ መቻሉ ተመላከተ፡፡ በዞኑ ባለፉት አስራ አንድ ወራት 10 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡን የዞኑ ገቢዎች ፅህፈት ቤት አስታውቋል። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ካሳሁን ታደለ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የገቢ ምንጭን ለማስፋት እና ግንዛቤን ለማሳደግ በተሰራው ስራ በዘንድሮው ዓመት ከዕቅድ በላይ ማከናወን ተችሏል። በዚህም በበጀት ዓመቱ 9 ነጥብ 4 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ 10 ነጥብ 9 ቢሊየን ብር በመሰብሰብ 116 በመቶ ከዕቅድ በላይ ማከናወን ተችሏል ብለዋል። ኃላፊው አክለውም ይህ ገቢ ከመደበኛ፣ መደበኛ ካልሆኑ እና ከማዘጋጃ ቤት አገልግሎት የተሰበሰበ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በዚህ ዓመት መንግስት የገቢ ምንጭን ለማስፋት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሠረት ለማዕከላዊ ገበያ ከሚቀርብ ቡና የተሻለ ገቢ መሰብሰቡን ተናግረዋል። በዞኑ ከ27 ሺህ በላይ የንግድ ተቋማት መኖራቸውን ጠቅሰው የመንግስት እና የግል ተቋማትን ጨምሮ ከልዩ ልዩ የገቢ ምንጮች በጥንቃቄ መሰብሰቡ እና የግብር ከፋዩ ግንዛቤ እያደገ መምጣቱ ለተገኘው ውጤት ዋና ምክንያት ነው ብለዋል። የገቢ አሰባሰብ ሂደት መዘመን እና በቴክኖሎጂ መታገዝ ለቁጥጥር ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የተናገሩት አቶ ካሳሁን ይህም አሰራሩን ቀላል አድርጎታል ብለዋል። በቀጣይም የማህበረሰቡን ግንዛቤ ይበልጥ በማስፋት የበለጠ ውጤታማ ለመሆን እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል።   የጅማ ከተማ ነዋሪ የሆኑት አቶ በፍቃዱ ታሪኩ፣ የግብር አከፋፈል ሂደቱ ከዚህ ቀደም ከነበረው ሁኔታ እጅግ የተሻሻለ መሆኑን ጠቅሰው በተለይም በቴክኖሎጂ የታገዘ መሆኑ ጊዜዬን ቆጥቦልኛል ብለዋል። የተሽከርካሪ ግብር ክፍያን በየጊዜው ገቢ እንደሚያደርጉ የሚናገሩት አቶ ሙሉቀን ጎሹ እና ጌታሁን ግርማ መንግስት ያስቀመጠው የግብር አከፋፈል ሂደት ምቹ እና ዘመናዊ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከዚህ ቀደም የነበሩ ችግሮች ተቀርፈው ግልፅነት በተሞላበት መልኩ የተሻለ አገልግሎት እያገኘን ነው ብለዋል።
የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና ጥራቱን ለማስጠበቅ የተከናወኑ ተግባራት የዘርፉን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እያሳደጉ ነው
Jun 18, 2026 240
ሃዋሳ፤ ሰኔ 11/2018(ኢዜአ)፦ የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና ጥራቱን ለማስጠበቅ የተከናወኑ ተግባራት ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እያሳደጉ መሆኑን የኢትዮጵያ ቡናና ሻይ ባለስልጣን አስታወቀ። ባለስልጣኑ በቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎች የቨርሚ ኮምፖስት ዝግጅትና በቡና ክላስተር አጠቃቀም ላይ ያተኮረ የልምድ ልውውጥ መድረክ በሃዋሳ ከተማ አካሂዷል።   የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አዱኛ ደበላ (ዶ/ር) እንደገለጹት የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና የቡና ጥራትን ለማስጠበቅ የተከናወኑ ተግባራት በዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እያሳደጉት ነው። ባለፉት ዓመታት በቡና ግብይት ስርአት ውስጥ የተደረጉ ሪፎርሞች ተጨባጭ ውጤት ማምጣታቸውን ጠቅሰው፣ የሪፎርም ሥራው የቡና ተፈጥሯዊ ጣዕም እንዲጠበቅና ገዢዎች ምርቱን በቀጥታ እንዲያገኙ አስችሏል ብለዋል። በዚህም ለዓለም ገበያ የሚቀርበው የቡና መጠንና ጥራት እያደገ መምጣቱን ጠቁመው፣ በዘንድሮው የምርት ዘመን ለዓለም ገበያ ከሚቀርበው ቡና 3 ቢሊየን ዶላር ለማግኘት ግብ ተይዞ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ዘንድሮ በዓለም ገበያ የቡና ዋጋ ቢወርድም የኢትዮጵያ ቡና ጥራት ደረጃ ጥሩ በመሆኑ በዓለም ገበያ ከአምናው በተሻለ ዋጋ መሸጡን ተናግረዋል። በመሆኑም የቡና ጥራትን ለማስጠበቅና ምርትና ምርታማነትን ይበልጥ ለማሳደግ በየአካባቢው ያሉ ምርጥ ተሞክሮዎችን የመቀመር ሥራ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የዛሬው መድረክም በሲዳማ ክልል በቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎችና በአርሶ አደር ማሳ የሚከናወነውን የቨርሚ-ኮምፖስት አዘገጃጀት ተሞክሮን በማስፋት በዘርፉ የሚገኘውን ጥቅም ለማሳደግ ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። የሲዳማ ክልል ቡና፣ ፍራፍሬና ቅመማቅመም ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር መስፍን ቃሬ በበኩላቸው በክልሉ የቡና ምርትና ምርታማነት ለማሳደግና ጥራቱን ለማስጠበቅ የአፈር ለምነት የመጠበቅ ሥራ እየተሰራ ነው።   በተለይም የተፈጥሮ ማዳበሪያ ላይ በማተኮር በቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎችና በአርሶ አደሮች ማሳ ቨርሚ ኮምፖስት የማዘጋጀት ሥራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። በዚህም ባለፉት ሁለት ዓመታት 220 የቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎች ቨርሚ ኮምፖስት በማዘጋጀት ለቡና አምራች አርሶ አደሮች እያቀረቡ መሆኑን ገልጸዋል። የቨርሚ ኮምፖስት የቡና ምርታማነትና ጥራትን በመጨመር መሬቱ ተከታታይ ምርት እንዲሰጥ ከማድረግ ባሻገር የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ጉልህ ድርሻ አለው ነው ያሉት። የክልሉ መንግስት የተገኘውን ተሞክሮ በማስፋት የቡና ምርትና ምርታማነትን የማሳደግና ጥራቱን የማስጠበቅ ስራ አጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉም አክለዋል። በመድረኩ ከተለያዩ ክልሎች የተውጣጡ የቡና ማዘጋጃ ኢንደስትሪዎች ተወካዮች፣ አርሶ አደሮችና የምርምር ተቋማት የተገኙ ሲሆን የሲዳማ ክልል ምርጥ ተሞክሮም ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። በቀጣይም በአርሶ አደር ማሳ እና በቡና ማዘጋጃ ኢንዱስትሪዎች የመስክ ምልከታና የልምድ ልውውጥ እንደሚደረግ ታውቋል።
በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን በዘንድሮው የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ከ2 ነጥብ 1 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ተገኝቷል
Jun 18, 2026 186
ደብረ ብርሃን፤ ሰኔ 11/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን በዘንድሮው በጋ መስኖ ከለማው ስንዴ ከ2 ነጥብ 1 ሚሊየን ኩንታል በላይ ምርት ማግኘቱ ተገልጿል። በዞኑ ግብርና መምሪያ የመስኖ አጠቃቀም አግሮኖሚስት ዘሩ ገረመው እንደገለጹት የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት አርሶ አደሩ በምግብ ራሱን ከመቻል ያለፈ ምርት እንዲያመርት አስችሏል። በበጋው ወራት የተለያዩ የመስኖ አማራጮችን በመጠቀም 51 ሺህ 966 ሄክታር መሬትን በስንዴ በማልማት ከ2 ሚሊየን 147 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ማግኘት መቻሉን ገልጸዋል። ምርታማነቱን ለማሳደግም በባለሙያዎች ድጋፍ የማዳበሪያ፣ የምርጥ ዘርና ሌሎች ቴክኖሎጂዎችን አርሶ አደሩ በአግባቡ እንዲጠቀም ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። በዚህም የዞኑ የበጋ መስኖ ስንዴ ምርታማነት በሄክታር በአማካይ 60 ኩንታል እንዲደርስ ማስቻሉን አስረድተዋል።   አርሶ አደሮቹ ያመረቱትን ስንዴ ከቤት ውስጥ ፍጆታ ባሻገር ለኢንዱስትሪዎች ግብዓትና ለአካባቢው ገበያ በማቅረብ የገበያ ማረጋጋት ስራ ማከናወናቸውን ተናግረዋል። በዞኑ የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ የሰብልና ኢንዱስትሪ ግብይት ባለሙያ ጌታው ሙሉ፤ በዞኑ በዘንድሮው በጋ በጥራትና በብዛት ስንዴን በማምረት ለገበያ እየቀረበ ነው ብለዋል። እስካሁንም 200 ሺህ ኩንታል የሚጠጋ የስንዴ ምርት በአካባቢው ለሚገኙ አንዱስትሪዎችና ሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት መቅረቡን ጠቁመው የገበያ ማረጋጋቱ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በዚህም አሁን ላይ የስንዴ ዋጋ መቀነሱን ጠቁመው ይህም የዱቄት ፋብሪካዎች በቂ ዱቄት በማምረት ለዳቦ አምራቾች እንዲያቀርቡ እድልን ፈጥሯል ብለዋል። በዞኑ በሲያደብርና ዋዩ ወረዳ አርሶ አደር ታፈሰ ቱሉ፤ የበጋ መስኖ ልማት ስራ ምርታማነታችንን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ ሃብት እንድንፈጥር አስችሎናል ነው ያሉት። በዘንድሮው በጋም አራት ተኩል ሄክታር ማሳቸው ላይ ከአካባቢው አርሶ አደሮች ጋር በመተባበር ስንዴን በኩታ ገጠም በማልማት ከ200 ኩንታል በላይ ምርት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። ያመረቱትን ምርትም በተፈጠረላቸው የገበያ ትስስር በአካባቢው ለሚገኙ አንዱስትሪዎች በማቅረብ የተሻለ ገቢ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ሌላው የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ደርቤ ፈለቀ በበኩላቸው አንድ ሄክታር ማሳቸውን በበጋ ስንዴ በማልማት 60 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን ገልፀዋል።
የኮሪደር ልማቱ የድሬዳዋን የተደበቀ ውበት በመግለጽ ከተማዋን ተመራጭ የስራና የመኖሪያ ማዕከል አድርጓታል
Jun 18, 2026 190
ድሬዳዋ፤ ሰኔ 11/2018(ኢዜአ)፦ የኮሪደር ልማቱ ታሪካዊ ቅርሶችን በጠበቀ መልኩ መከናወኑ ድሬዳዋን ተመራጭ የኢንቨስትመንትና የቱሪስት መዳረሻ እያደረጋት መሆኑን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የከተማዋ አመራሮችና ነዋሪዎች ገለጹ። በድሬዳዋ ከተማ የሚገኙ ጥንታዊ ህንጻዎች፣ ልዩ የሥነ-ህንጻ ጥበብ እና የህዝቦቿ የባህል ብዝሃነት የቱሪስት መስህብ ሆነው መቆየታቸው ይታወቃል።   በአሁኑ ወቅት በመንግስት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት በሀገሪቱ ዋና ዋና ከተሞች እየተተገበረ የሚገኘው የኮሪደር ልማት፣ የከተማዋን ገጽታ በማዘመን፣ መንገዶቿን በማስፋትና ለነዋሪዎች ምቹ አካባቢን በመፍጠር ከፍተኛ ለውጥ እያመጣ ነው። የኮሪደር ልማቱ የድሬዳዋን ታሪካዊ ማንነት ጠብቆ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ዘርፍ አዲስ መነቃቃትን እየፈጠረ መሆኑን የአካባቢው አመራሮችና ነዋሪዎች ገልጸዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር በፕሮጀክት ፅህፈት ቤት የኮሪደር ልማት አስተባባሪ ወንድወሰን ጀንበሬ እንደተናገሩት፤ በአምስት አቅጣጫዎች የተከናወነው የኮሪደር ልማት የከተማዋን ገፅታና ውበት አጉልቶ አውጥቷል። በተለይም የከተማዋን ታሪካዊ ቅርሶችና ሃብቶች በጠበቀ መልኩ መከናወኑ ከተማዋን ዘመናዊ የኑሮና የስራ ተመራጭ ማዕከል እያደረጋት መሆኑን ጠቅሰዋል። በኮሪደር ልማቱ የተካተቱት ዘመናዊ መንገዶች፤ የመዝናኛ ማዕከላትና ሌሎች መሠረተ ልማቶች ድሬዳዋን ይበልጥ የኢንቨስትመንት መዳረሻ እያደረጋት ይገኛልም ብለዋል።   የአስተዳደሩ ባህልና ቱሪዝም ፅህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ነኢማ ኢብራሂም በበኩላቸው፤ የኮሪደር ልማቱ የቱሪዝም መዳረሻ የሆኑትን ሰው ሰራሽ እና የተፈጥሮ ሃብቶች ይበልጥ ማጉላቱን ገልጸዋል። በተለይም ለድሬዳዋ ከተማነት መሠረት በጣለውና የቱሪስት መዳረሻነት እያገለገለ በሚገኘው ታሪካዊ የባቡር ጣቢያ ጋር ተዋህዶ የተሰራው ልማት ቅርሱን ቱሪስቶች ይበልጥ እንዲጎበኙት እያደረገ ይገኛል ነው ያሉት። ከቱሪዝም መዳረሻዎች ባሻገር የነዋሪውን ትስስርና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲጠናከር ምቹ መደላድል መፍጠሩን በመጠቆም። ሌላው አስተያየት ሰጭ ሼህ አብዶ ኡመር፤ የኮሪደር ልማቱ የተደበቀውን የድሬዳዋን ውበትና ገፅታ በመግለጽ ነዋሪውን ያስደሰተ መሠረታዊ ስራ መሆኑን ተናግረዋል።   የኮሪደር ልማቱ የድሬዳዋን የአስፋልት፣ የእግረኛ እና የብስክሌት መንገዶችን ማስፋቱ የትራፊክ መጨናነቅና አደጋን በመቀነስ በኩል መሠረታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ያሉት ደግሞ ሌላው ነዋሪ አቶ ሀብታሙ አሰፋ ናቸው። በተለይም የተፈጠሩት የመዝናኛና የአረንጓዴ ቦታዎች ለአረጋውያንና ለልጆች መዝናኛ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጠና ማህበራዊ መስተጋብርን እንደሚያዳብር አንስተዋል።   የከተማ አስተዳደሩ እያከናወናቸው ካሉ የኮሪደር ልማት ስራዎች በተጓዳኝ የግል ተቋማትም ከተማዋን በማደስና በማስዋብ በኩል ከአንድ ቢሊየን ብር በላይ ወጪ ማድረጋቸውን ከአስተዳደሩ የፕሮጀክት እና የኮሪደር ልማት ፅህፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን የፍራፍሬ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው
Jun 18, 2026 163
ጊምቢ፤ ሰኔ 11/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ዞን ከቡና ልማት ጎን ለጎን የፍራፍሬ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። በዞኑ በበጀት ዓመቱ ከ2 ነጥብ 3 ሚሊየን ኩንታል በላይ የፍራፍሬ ምርት መሰብሰቡም ተመላክቷል። በጽሕፈት ቤቱ የፍራፍሬ ልማት ባለሙያ ጂብሪል መንጌ እንዳስታወቁት፤ ዞኑ በስፋት ከሚታወቅበት የቡና ልማት ጎን ለጎን በፍራፍሬ ልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ።   ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ተግባራዊ የተደረገው የፍራፍሬ ልማትም የአርሶ አደሩን የሥራ ባህል በመቀየር በኩል አበረታች ውጤት ማስገኘቱን ተናግረዋል። ልማቱ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የምግብ ሥርዓትን ከማሻሻል አንጻር የላቀ ሚና እንዳለው ጠቁመው፤ ይህንን ታሳቢ ያደረገ እንቅስቃሴ በየደረጃው ሲካሄድ መቆየቱን አውስተዋል። በአሁኑ ወቅት 41 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ መሬት የፍራፍሬ ምርት መስጠት በሚችልበት ደረጃ ላይ የደረሰ ሲሆን፣ ከዚህም 2 ሚሊየን 399 ሺህ 710 ኩንታል የፍራፍሬ ምርት ተሰብስቦ ለገበያ ቀርቧል ብለዋል። ለገበያ ከቀረቡት የፍራፍሬ ምርቶች መካከል አናናስ፣ ሙዝ፣ ማንጎ፣ አቮካዶ፣ ፓፓያና ብርቱካን ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውን ገልጸው፤ የተሻሻለ የአቮካዶ ዝርያ ምርት ለውጭ ገበያ የሚቀርብ በመሆኑ፣ የአካባቢው አርሶ አደሮች ተጠቃሚነት እያደገ መምጣቱንም ተናግረዋል።   በዚህ ዓመትም የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማሳደግ፤ ልማቱን ከአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ጋር በማቀናጀት የፍራፍሬ ችግኞችን በብዛትና በጥራት ለተከላ እየተዘጋጀ መሆኑን። የልማቱ ተሳታፊ የሆኑት የላሎ አሳቢ ወረዳ አርሶ አደር ታረቀ ጂሬኛ፤ ከዚህ ቀደም ሕይወታቸውንና ገቢያቸውን በቡና ልማት ላይ ብቻ መስርተው እንደነበር አስታውሰዋል። ሆኖም መንግሥት ያመቻቸላቸውን የፍራፍሬ ችግኝና ምርጥ ዘር በመጠቀም በዘርፉ መሰማራታቸውንና ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት በይዞታቸው ላይ ሙዝ፣ አቮካዶ እና አናናስ በማልማት በዓመት የተሻለ ገቢ እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላው የሆማ ወረዳ አርሶ አደር ገረመው ጂሩ በበኩላቸው፤ ከግብርና ምርምር ማዕከል የወጣ የተሻሻለ የሙዝ ዝርያን በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል። ምርቱን ለአካባቢው ገበያ በማቅረብ በአንድ ዙር እስከ 30 ሺህ ብር ገቢ እያገኙ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይም ልማቱን በማጠናከር አቮካዶና ሙዝ በስፋት ለማልማት ማቀዳቸውን አስታውቀዋል።
የንግድ ምክር ቤቶችና ማህበራት ለህዝብ ያላቸውን ተደራሽነት በመጠቀም ለምክክሩ አሳታፊነትና አካታችነት ሚናቸውን መወጣት አለባቸው
Jun 17, 2026 791
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018(ኢዜአ)፦ የንግድ ምክር ቤቶችና ማህበራት ለህዝብ ያላቸውን ተደራሽነት በመጠቀም ለሀገራዊ ምክክሩ አካታችነትና አሳታፊነት ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባዬ ኦጋቶ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ከሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጋር በመተባበር "በሀገራዊ ምክክር ሂደት የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ" በሚል መሪ ሀሳብ በሀገራዊ ሰላምና መረጋጋት ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ አዘጋጅቷል፡፡   የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ከባቢ ለመፍጠር በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የግሉን ዘርፍ በመወከል ከመንግሥት ጋር ምክክር የሚያደርግ ተቋም ነው። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባዬ ኦጋቶ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የብዝሀነትና የዕምቅ አቅም ባለቤት ብትሆንም ለዘመናት ከግጭት አዙሪት መውጣት አቅቷት ቆይታለች። ስለሆነም የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዜጎች ያልተግባቡባቸውን ዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች በምክክር መፍታት የሚችሉበትን አውድ መፍጠሩን ገልጸዋል። ኮሚሽኑ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እንዲወያዩና ለችግሮች የጋራ መፍትሔ ለመፈለግ የተቋቋመ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት ኢትዮጵያውያን በነፃነት የሚነጋገሩበትን አውድ መፍጠር፣ የልዩነት መንስኤ የሆኑ አጀንዳዎችን መለየት እና በሂደቱ ላይ የሚወያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በመለየት ውጤታማ ሥራዎችን ማከናወኑን ገልጸዋል፡፡ የምክክር ሂደቱ ከጅምሩ አካታችና ሁሉን አቀፍ መሆኑን ገልጸው፤ ነጋዴዎችና የንግድ ተቋማት ባለቤቶች ከቀበሌ ጀምሮ እስከ ፌዴራል ድረስ በንቃት በመሳተፍ ሂደቱን ሲያሳልጡ ቆይተዋል ብለዋል፡፡ የንግድ ምክር ቤቶችና የንግዱ ማህበረሰብ ከተሳታፊነት ባለፈ በባለቤትነት ትልቅ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ተናግረዋል፡፡ የንግድ ምክር ቤቶችና ማህበራት ለህዝብ ያላቸውን ተደራሽነት በመጠቀም ለሀገራዊ ምክክሩ አካታችነትና አሳታፊነት ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባም ነው የገለጹት፡፡ የንግዱ ማህበረሰብ የሰላምን፣ የመቻቻል፣ የመግባባትና የአንድነት ትርክት በመፍጠር አምባሳደር መሆን ይችላል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ከህዝብ ጋር ባላቸው ቀረቤታ ተግባራዊ ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡ የንግዱ ማህበረሰብ ለዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ከፍተኛ ሚና እንዳለው በመጥቀስ፣ በቀጣይ በዋናው የምክክር ጉባኤ ላይ የህዝቡን ተሳትፎ በማጎልበትና የባለቤትነት ሚናቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡   የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ዓይናለም አባይነህ (ዶ/ር)፤ በኢትዮጵያ ዘላቂነት ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት ለማስመዝገብ አስተማማኝ ሰላም ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የጀመረው ሂደት በኢትዮጵያ ለንግዱ ማህበረሰብ ምቹ የንግድና ኢንቨስትመንት ምህዳር መፍጠር እንደሚያስችልም ገልጸዋል፡፡ የንግዱ ማህበረሰብ የግሉን ዘርፍ በመወከል ለምክክር ሂደቱ ስኬት የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ ገልጸው፤ ምክክሮች ወደ ተጨባጭ ውጤቶች እንዲቀየሩ የበኩላቸውን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩም አረጋግጠዋል። የምክክር ኮሚሽኑ የጀመረው የምክክር ሂደት የጋራ እይታና የጋራ ልማት የሚያመጣ በመሆኑ ይህንኑ ጥረት በመደገፍ በንቃት እንደሚሳተፉ ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ የንግድና ዘርፍ ማህበራት እና የአማራ ክልል ንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤቶች የቦርድ አባል እስማኤል አሊ፤ ችግሮችና አለመግባባቶች በውይይት ቢፈቱ የመጀመሪያው ተጠቃሚ የንግዱ ማህበረሰብ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እንደ ንግድ ማህበረሰብ ከቀበሌ ጀምሮ አጀንዳዎቻቸውን እያስያዙ በንቃት ሲሳተፉ እንደነበር ገልጸው፤ መወያየትና መመካከር ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የንግድና ዘርፍ ማህበራት ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ቦጋለ ቢታኒ በበኩላቸው፤ የምክክር ሂደቱ በሰፊው የተሳተፉበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የምክክር ኮሚሽኑ ሥራዎች የላቁ መሆናቸውን ገልጸው፤ የሰላሙ ባለቤት የሆነው የንግዱ ማህበረሰብ አስፈላጊውን ሁሉ ለማድረግ ዝግጁ ነው ብለዋል፡፡
የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ታሳቢ ያደረገው የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባሻገር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ነው
Jun 17, 2026 415
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018(ኢዜአ)፦የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ታሳቢ ያደረገው የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ ባሻገር የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ነው ሲል በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የግብርና ቢዝነስ ኩባንያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የሕዝብ እና የባለድርሻ አካላት ይፋዊ የውይይት መድረክ አካሂዷል።   የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ላሌ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ግብርና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እድገት፣ የኢንዱስትሪ ልማት እና የሥራ ዕድል ፈጠራ ዋነኛ መሠረት ነው። ስለሆነም ኋላቀር ከሆነው የግብርና አሠራር በማላቀቅ ወደ ዘመናዊ፣ ተወዳዳሪ እና ገበያ መር ሥርዓት ማሻገር እንደሚገባ ገልጸዋል። ይህ ረቂቅ አዋጅ ሲጸድቅ አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮች እና ከፊል አርሶ አደሮችን በኩባንያ በማደራጀት የመጠቀም መብታቸውን የሚያረጋግጥ ይሆናል ብለዋል። እንዲሁም የእንስሳት ሀብታቸውን እና ጉልበታቸውን ወደ ካፒታል በመለወጥ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የሚያስችል እንደሆነም ገልጸዋል።   የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ በዚሁ ወቅት፤ የግብርና ትራንስፎርሜሽንን ማረጋገጥ የመንግሥት ዋና ትኩረት በመሆኑ ለዚህም በርካታ የፖሊሲ፣ የፕሮግራም እና የተቋም ሪፎርም ሥራዎች በሀገር ደረጃ እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። ይህ ረቂቅ አዋጅ ግብርናን ለማሸጋገር ከሚከናወኑ የሪፎርም ሥራዎች መካከል ዋነኛው ሲሆን፤ አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ የሀገር ውስጥ ኩባንያዎችን እና ካምፓኒዎችን እንዲመሰርቱ ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡ አርብቶ አደሩን በማደራጀት፣ የእንስሳት ዝርያዎችን በማሻሻል እና የጤና አጠባበቅን በማዘመን፣ አርብቶ አደሩ የራንች ባለቤት እንዲሆንና ሥራዎቹን በባለቤትነት እንዲያከናውን ለማድረግ ታሳቢ ያደረገ ረቂቅ አዋጅ እንደሆነ ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ማንደፍሮ ንጉሤ እንደተናገሩት፤ ረቂቅ አዋጁ አርሶ አደሩን ወደ ኩባንያ አደረጃጀት በማሸጋገር የኢኮኖሚ እድገትን ይበልጥ ሊያፋጥኑ የሚችሉ አዳዲስ አቅሞችን መፍጠር ያስችላል ብለዋል። ሂደቱ አርሶ አደሮች ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን በምጣኔ ሀብት ከመደገፍ ባለፈ፤ በሀገሪቷ የኢኮኖሚ መዋቅር ውስጥ ግንባር ቀደም ተዋናይ እንዲሆኑ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ገልጸዋል። በመጪዎቹ አምስት እና አስር ዓመታት ውስጥ አርሶ አደሮቹን ወደ ከፍተኛ ደረጃ በማሸጋገር ድንበር ተሻጋሪ የንግድ ሥራዎችን የሚያከናውኑና በዓለም አቀፍ ገበያ ተወዳዳሪ የሆኑ ትላልቅ የወጪ ንግድ ነጋዴዎች ይሆናሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። በውይይቱ የተሳተፉት ባለድርሻ አካላት ረቂቅ አዋጁ እንደሀገር የተያዘውን የገጠር ትራንስፎርሜሽን ከግብ የሚያደርስ ነው ብለዋል። አነስተኛ ይዞታ ያላቸው አርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ተጠቃሚ እና አሳታፊ የሆነ ሥርዓት እንደሚዘረጋ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖረው ተናግረዋል።  
በጅማ ዞን በሌማት ትሩፋት የተሰማሩ ወጣቶች ውጤታማ እየሆኑ ነው
Jun 17, 2026 363
ጅማ፣ሰኔ 10/2018(ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ጅማ ዞን በሌማት ትሩፋት የተሰማሩ ወጣቶች ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናገሩ። የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ከተተገበረ ጀምሮ በጅማ ዞን በርካታ ዜጎች ተጠቃሚ መሆን መቻላቸው ተገልጿል። መርሃ ግብሩ በተለይም ወጣቶች ከራስ አልፈው ለማህበረሰቡ የሚተርፍ ምርት እንዲያመርቱ ከማስቻሉም በላይ፣ የብዙዎችን የስራ አጥነት ችግር በዘላቂነት እየቀረፈ ይገኛል። በዞኑ ጮራ ቦቶር ወረዳ ነዋሪ የሆነው ወጣት አሸናፊ ባጊዴ እና ጓደኞቹ ተደራጅተው በዶሮ እርባታ ስራ ላይ በመሰማራት ውጤታማ መሆን የቻሉ ወጣቶች ናቸው። ወጣት አሸናፊ እንደሚያብራራው፣ ወጣቶቹ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ ለረጅም ጊዜ ምንም አይነት የስራ እድል አላገኙም ነበር።   በመንግስት በተደረገላቸው ድጋፍ በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር ስር በዶሮ እርባታ የተሰማሩት እነዚህ ወጣቶች፤ በአሁኑ ወቅት በቀን ከሺህ በላይ እንቁላል ለገበያ እያቀረቡ ይገኛሉ። በዚህም በአጭር ጊዜ ውስጥ በመጀመሪያው ዙር ብቻ ከ100 ሺህ ብር በላይ መቆጠብ መቻላቸውን ገልጸዋል። ሌላኛው የዚሁ ወረዳ ነዋሪ የሆነው ወጣት አብዱላቂ አደም በሙዝ ልማት ላይ ተሰማርቶ ስኬታማ መሆን ችሏል። የግብርና ባለሙያዎች ያቀረቡለትን የተሻሻለ የሙዝ ዝርያና ሙያዊ እገዛ በመጠቀም፣ ምርቱን በስፋት ለገበያ እያቀረበ መሆኑን ተናግሯል። ከሚያገኘው ገቢ ራሱንና ቤተሰቡን ከመደገፍ ባለፈ፣ ለአራት የአካባቢው ወጣቶች ተጨማሪ የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ገልጿል። በሊሙ ኮሳ ወረዳ በዘንድሮው አመት በከብት ማድለብ ስራ ላይ የተሰማሩት ወጣት ሁሴን አባዱራ እና ጓደኛውም በተመሳሳይ ውጤታማ እየሆኑ መሆናቸውን ይናገራሉ። "ከዚህ ቀደም ምንም አይነት ስራ አልነበረንም፤ የከተማ አስተዳደሩ ባመቻቸልን የስራ እድል ተጠቅመን ወደ ስራ በመግባታችን በአጭር ጊዜ ውስጥ ራሳችንን ችለን ለሌሎችም የስራ ዕድል መፍጠር ችለናል" ብለዋል።   የጅማ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቲጃኒ ተማም እንደገለጹት፤ በዞኑ በየአመቱ የሌማት ትሩፋት ተጠቃሚዎች ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ እየጨመረ መጥቷል። ዘርፉ ለበርካቶች የስራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ ማህበረሰቡ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ እያገዘ መሆኑን ጠቅሰው፤ በአሳ እና ከብት ዕርባታ፣ በንብ ማነብ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ምርት እንዲሁም በዶሮ እርባታ የመርሃ ግብሩ ዋና ዋና ዘርፎች ናቸው ብለዋል። በዞኑ በዘንድሮው አመት 314 ሺህ ሰዎችን የሌማት ትሩፋት ተሳታፊ ለማድረግ ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ እቅዱን በማሻገር ከ339 ሺህ በላይ ዜጎችን የመርሃ ግብሩ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የጽህፈት ቤት ኃላፊው ገልጸዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም