አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያሳደገ ነው
Jul 9, 2026 427
ደብረ ብርሃን፤ ሐምሌ 2/ 2018(ኢዜአ):- የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የነዋሪዎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደገ መሆኑን በአማራ ክልል የሰሜን ሸዋ ዞን ግብርና መምሪያ አስታወቀ። መምሪያው "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሃሳብ የክረምቱን የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ የማስጀመሪያ መርሃ ግብር በሲያደብርና ዋዩ ወረዳ "ጋራ መየ" ተፋሰስ ዛሬ አካሂዷል። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ታደሰ ማሙሻ እንዳሉት ፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የለሙ ተፋሰሶች አርሶ አደሩ ከእለት ፍጆታው ያለፈ ምርት ለማምረት የሚያስችለውን አቅምን ፈጥሮለታል። በዋናነትም በመኖ ልማት፣ በእንስሳት እርባታና ማድለብ፣ በንብ ማነብ ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ዘርፎች እንዲሰማሩ ማስቻሉን ገልጸዋል። በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በዞን ደረጃ በ36 ሺህ 284 ሄክታር መሬት ላይ ከ298 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል ነው ያሉት። በዘንድሮው ዓመት የሚተከሉት ችግኞች የዞኑን የደን ሽፋን ከፍ ለማድረግ የሚያስችል ነው ብለዋል። በክረምቱ ሁለት ነጥብ አራት ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኞችን በመትከል የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማሳደግ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መካሻ ዓለማየሁ በበኩላቸው ፤ህብረተሰቡ በየዓመቱ ችግኝ በመትከል ምርታማነትን በዘላቂነት ለማሳደግ የጀመረውን ስራ አጠናክሮ መቀጠል ይገባዋል ሲሉ አሳስበዋል ። የሚተከሉ ችግኞችም አሁን ያለውን አርሶ አደርና ወጣት ተጠቃሚ ከማድረግ ባሻገር የመጪውን ትዉልድ ታሳቢ ባደረገ መልኩ እየተከናወነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የሲያ ደብርና ዋዩ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ደሱ ምክረ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የሚተከሉ ችግኞች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸዉና ለአካባቢ ስነ ምህዳር ጥበቃ ከፍተኛ ፋይዳ የሚያበረክቱ ናቸው። በወረዳው በያዝነው ክረምት ስምንት ነጥብ አራት ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል የሚያስችል የቦታ ዝግጅት ተካሂዶ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል። የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ዓለማየሁ ያዴቴ እንደገለጹት፤በዘንድሮው ዓመት ከዚህ በፊት ከተከሏቸው ችግኞች 30 ሺህ ብር ገቢ ማግኘታቸውን ጠቁመዋል ። የተተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ የጽድቀት ምጣኔያቸውን ለማሳደግ እንሰራለን ሲሉም ገልጸዋል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይም ከዞንና ከወረዳ የተውጣጡ ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በክረምቱ ወቅት በሁለት ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የፍራፍሬ ልማት ይካሔዳል
Jul 9, 2026 220
ደብረ ማረቆስ ፤ሃምሌ 2/2018(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን በዘንድሮው ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ሁለት ሺህ ሄክታር መሬት የሚሸፍን የፍራፍሬ ልማት እንደሚካሔድ የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለፀ። በመምሪያው የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ባለሙያ አቶ ተሾመ በላይ ለኢዜአ እንደገለጹት፤በተያዘው ክረምት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከአንድ ሚሊዮን በላይ የፍራፍሬ ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል። ለተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች ውስጥ የአቮካዶ፣ ብርቱካን ፣ ማንጎ ፣ ሎሚ ፣ ፓፓያ እና የአፕል ዝርያዎች እንደሚገኙበት ነው ያመለከቱት። የችግኝ ተከላው በሁለት ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የሚካሔድ ሲሆን እስካሁን በተደረገው ጥረት ከ80 ሺህ በላይ የፍራፍሬ ችግኝ መተከሉን ገልፀዋል ። በዚሁ የፍራፍሬ ችግኝ ተከላ ከ20 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን እንደሚሳተፉም ነው ያመለከቱት። በአሁኑ ወቅትም አርሶ አደሩ ከሰብል ልማት ጎን ለጎን በፍራፍሬ ልማት ተሳትፎ ተጠቃሚነቱን እንዲያረጋግጥ የተሻሉ ስራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል። ለአብነትም ባለፉት ጥቂት ዓመታት ቡናን ጨምሮ ሌሎች የፍራፍሬ አይነቶችን በማልማት አርሶ አደሩ ቋሚ ገቢ በማግኘት ጥሪት እንዲያፈራ እየተደረገ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በየደረጃው ያለው የዘርፉ አመራርና በላሙያም አርሶ አደሩን በመደገፍ እያደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን አስገንዝበዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት ጥቂት ዓመት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ20 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በፍራፍሬ ልማት መሸፈኑን ከዞኑ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በአቮካዶ ምርት የተመዘገበውን ስኬት በቆላ ፍራፍሬ ልማት ለመድገም እየተሰራ ነው
Jul 8, 2026 477
ገንዳ ፤ ሐምሌ 1/ 2018 (ኢዜአ):- የአቮካዶ ምርትን ወደ ውጭ በመላክ እየተመዘገበ ያለውን ስኬት በሌሎች የቆላ የፍራፍሬ ልማቶች ለመድገም የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የምዕራብ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በምዕራብ ጎንደር ዞን "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሃሳብ የአረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በዞኑ በገንዳውኃ ጊዮርጊስ ተፋሰስ ተጀምሯል። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊና ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አንዳርጌ ጌጡ እንደገለጹት ፤ለዘንድሮው ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከአንድ ነጥብ አምስት ሚሊዮን በላይ ችግኞች በማዘጋጀት የተከላ ስራ ተጀምሯል። ለተከላ የተዘጋጁት ችግኞችም ለምግብነት የሚውሉ፣ ቀጥተኛ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የደን ዝርያዎችና ለእንስሳት መኖ የሚውሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዞኑ ለቆላ ፍራፍሬ ልማት ያለውን ምቹ የአየር ንብረት፣ ለም መሬትና ከፍተኛ የውሃ አማራጭ በመጠቀም የተሻለ ውጤት ለማምጣት በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። "ለፍራፍሬ ልማት ቀደም ብለን ተዘጋጅተናል" ያሉት ኃላፊው ከ200 ሺህ በላይ የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች በክላስተር መዘጋጀቱን ጠቁመው ከ600 ሺህ በላይ የሙዝ፣ ማንጎ ፣ ዘይቱን ፓፓያና ብርቱካን ችግኞች ይተከላሉ ብለዋል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ በበኩላቸው “ተስፋን እንትከል” በሚል መሪ ቃል በተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ላይ የዞኑ ሕዝብ በንቃት በመሳተፍ ተጠቃሚነቱን እንዲያሳድግ አሳስበዋል። ችግኞችን ከመትከል ባለፈ፣ በዘላቂነት ፀድቀው ለታለመላቸው ፍሬ እንዲበቁ ተገቢውን እንክብካቤ ማድረግ እንደሚገባም ነው ያመለከቱት። በመርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉት ወጣት አሸናፊ ታፈረና ደጉ ገብረ እግዚአብሔር በበኩላቸው፣በአረንጓዴ አሻራ የተተከሉ ችግኞች በአጭር ጊዜ ለውጥ ማምጣታቸውን እንደተመለከቱ ተናግረዋል። እየተገኘ ያለውን ጥቅም ለማሳደግም በክረምቱ በሚካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ያለምንም ቀስቃሽ በፈቃዳቸው በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን አስረድተዋል። በማስጀመሪያው መርሐግብሩ ላይ የዞኑ የሥራ ኃላፊዎች፣ የመከላከያ ሰራዊት ከፍተኛ መኮንኖች፣ የፌዴራል ፖሊስ አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
የአረንጓዴ አሻራ እያስገኘ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል
Jul 7, 2026 619
ጎንደር፤ሰኔ 30/2018 (ኢዜአ):- የአረንጓዴ አሻራ መርሃ- ግብር እያስገኝ ያለውን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የማስቀጠል ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የጎንደር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኜው ገለጹ። ከተማ አስተዳደሩ የክረምት የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በአዘዞ ክፍለ ከተማ በአባ ሳሙኤል ፓርክ ዛሬ አስጀምሯል። ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው አቶ ቻላቸው ዳኜው በዚሁ ወቅት እንደገለጹት ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ- ግብር ባጭር ጊዜ ውስጥ ዘርፈ ብዙ እና ተጨባጭ ለውጥ ለማስመዝገብ ያስቻለ ነው። በመርሃ- ግብሩ የለሙ ተፋሰሶች አርሶ አደሩ በመስኖ፣ በእንስሳት እርባታና ማድለብ፣ በንብ ማነብ ፣ በመኖና ሌሎች የልማት ዘርፎች በመሳተፍ ተጠቃሚ መሆን የቻለበት ነው ሲሉ ገልፀዋል። በተለይም በአትክልት እና ፍራፍሬ ልማት አርሶ አደሩ ዘላቂና ተጨማሪ ሃብት እንዲያፈራ መርሃ ግብሩ ሰፊ እድል ለመፍጠር እያስቻለ መሆኑንም ነው ያነሱት። በመሆኑም በዘንድሮው ዓመትም የአትክልት ፍራፍሬና ሌሎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ላይ በማተኮር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር እንደሚካሔድ አስረድተዋል። የከተማ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አበራ አደባ ፤በበኩላቸው በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ476 ነጥብ 5 ሔክታር መሬት ላይ 4 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞች እንደሚተከሉ ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት በተካሄደው መርሃ ግብርም 758 ሺህ ዜጎችን በአትክልት እና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተው ተጠቃሚ መሆናቸውን ነው የተናገሩት። በዘንድሮ ዓመትም ባለፉት ዓመታት የተገኘውን ተጠቃሚነት ለማስፋትም 500 ሺህ የአቡካዶ፣ ሙዝ፣ ማንጎና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን አስገንዝበዋል። የተተከሉ ችግኞችን የመጽደቅ ምጣኔ 95 በመቶ ለማድረስ ማህበረሰቡን ያሳተፈ የእንክብካቤና ጥበቃ ስራ እንደሚከናወን አስገንዝበዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ለእንስሳት መኖ፣ ለንብ ማነብ፣ ለከብት ማድለብና በወተት ልማት ዘርፍ እድገት ማስመዝገብን ጨምሮ ስርአተ ምግብም እንዲሻሻል ማድረጉን አስረድተዋል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ የኮፕ 32 ፕሬዝዳንት ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) ከኮፕ 30 ፕሬዝዳንት ጋር ተወያዩ
Jul 6, 2026 998
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29/2018(ኢዜአ)፡-የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ የኮፕ 32 ፕሬዝዳንት ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) ከ30ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ(ኮፕ 30) ፕሬዝዳንት አምባሳደር አንድሬ አራንሃ ኮሪያ ዶ ላጎ እና ከቡድናቸው ጋር ውይይት አድርገዋል። ኢትዮጵያ 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (COP32) አስተናጋጅ ለመሆን በምታደርገው ዝግጅት ላይ፣ ከቀደምት አዘጋጅ ሀገራት ልምድ መቅሰም ዋነኛው የትኩረት አቅጣጫ ሆኗል። በዚህም መንፈስ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የኢትዮጵያ የኮፕ 32 ፕሬዝዳንት ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) ከኮፕ 30 ፕሬዝዳንት አምባሳደር አንድሬ አራንሃ ኮሪያ ዶ ላጎ እና ከቡድናቸው ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አድርገዋል። የውይይቱ ዓላማ ዓለም አቀፉን የአየር ንብረት ጉባኤ ከማዘጋጀት ጋር የተያያዙ ዕውቀቶችን እና የተወሰዱ ትምህርቶችን መለዋወጥ መሆኑን ተመላክቷል።
በአፍሪካ የግብርና ትራንስፎርሜሽንን ለማፋጠን ጠንካራ የዕፅዋት ጤና ጥበቃ ሥርዓት መገንባት ይገባል
Jul 6, 2026 672
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29/2018(ኢዜአ)፦ በአፍሪካ አህጉር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ፣ የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ውጤታማ የዕፅዋት ጤና ጥበቃ ሥርዓት መገንባት ወሳኝ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። "የእፅዋት ሀብቶችን እና ተቋማትን ለመጠበቅ የአፍሪካ ሀገራትን በሳይንስ እና በዲጂታል መሳሪያዎች ማብቃት" በሚል መሪ ኃሳብ የተዘጋጀው የአፍሪካ ዕፅዋት ጤና ጥበቃ ፕሮግራም የስትራቴጂክ አጋርነት መድረክ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ አፍሪካ ግብርናውን ለመለወጥና ዘላቂ ልማት ለማምጣት የምታደርገው ጥረት በድንበር ተሻጋሪ ተባዮች፣ በወራሪ ዝርያዎች፣ በድንገተኛ በሽታዎች እና በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ከፍተኛ አደጋ ተደቅኖበታል። እነዚህ ተግዳሮቶች በምርት፣ በብዝሃ ሕይወት እና በኢኮኖሚ ዕድገት ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ የሚያሳድሩ በመሆናቸው፣ በእፅዋት ጤና ላይ መዋዕለ ነዋይ ማፍሰስ ለአፍሪካ የኢኮኖሚ ስኬት መሠረት መሆኑን ገልጸዋል። ተባይና የእፅዋት በሽታዎች በድንበር የማይገደቡ በመሆናቸው፣ የትኛዋም ሀገር ተግዳሮቶቹን ብቻዋን መፍታት ስለማይቻል አህጉራዊ የጋራ ርብርብ ያስፈልጋል ብለዋል። ጠንካራ የዕፅዋት ጤና ጥበቃ ሥርዓት መገንባት የግብርና ኢንቨስትመንቶችን ለመጠበቅ፣ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እና የተፈጥሮ ሥነ-ምህዳርን ለመንከባከብ መሠረታዊ መሆኑን አስገንዝበዋል። በተጨማሪም ደህንነቱ የተጠበቀና ተወዳዳሪ የንግድ ሥርዓትን ለማመቻቸት እንዲሁም የምግብ ሥርዓትን የመቋቋም አቅም ለማጠናከር ወሳኝ ሚና እንዳለው ጠቁመዋል። በኢትዮጵያም ዘላቂ የግብርና ትራንስፎርሜሽንን ለማምጣት የዕፅዋትን ጤና የመጠበቅ ተግባር ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሠራበት እንደሚገኝ አስታውቀዋል። የዓለም አቀፉ የዕፅዋት ጥበቃ ኮንቬንሽን ጸሃፊ ኤንሪኮ ፔሮቲ በበኩላቸው ድርጅቱ ጠንካራ እና የበለጠ የመቋቋም አቅም ያለው የዕፅዋት ጤናን ለመገንባትና የምግብ ዋስትናን ለመደገፍ በቁርጠኝነት እንደሚሠራ ገልጸዋል። አጋርነቶችን ማጠናከርና አዳዲሶችን መፍጠር እንደሚገባ ገልጸው፣ በአፍሪካ የዕፅዋት ጤና ፕሮግራም በኩል የተመዘገበው አስደናቂ እድገት በዓለም አቀፍ ደረጃ የላቀ ተፅዕኖ ለመፍጠር መሠረት መሆኑን ማረጋገጥ እንደሚገባ ተናግረዋል። የአፍሪካ ህብረት ኢንተር-አፍሪካን የዕፅዋት ጤና ጥበቃ ምክር ቤት አስተባባሪ ሳሊው ኒያሲ (ዶ/ር)፤ ተቋማቸው ለብሔራዊ ተቋማት የክትትል፣ የላቦራቶሪ ምርመራና የመከላከል አቅምን በማሳደግ፤ በሳይንስ ላይ የተመሠረተ ውሳኔ አሰጣጥንና ቀጣናዊ የመረጃ ልውውጥን እያጠናከረ ይገኛል ብለዋል። ይህ ፕሮግራም የአፍሪካ ህብረትን የዕፅዋት ጤና ስትራቴጂ ትግበራ የሚደግፍ እና በአካታች የአፍሪካ ግብርና ልማት ፕሮግራም ስር የተገለጹትን የአጀንዳ እ.አ.አ 2063 ለማሳካት እየተሰሩ ካሉት ስራዎች አንዱ መሆኑን ጠቁመዋል። በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የምግብ እና የእርሻ ድርጅት ጊዜያዊ ተወካይ ኦርላንዶ ሶሳ በበኩላቸው፣ ለስኬቱ የመንግስታት፣ የቀጣናዊ ድርጅቶች፣ የልማት አጋሮች፣ የቴክኒክ ተቋማት እና የግሉ ዘርፍ የተቀናጀ አጋርነት እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። የገንዘብ ድጋፍ፣ የቴክኒክ እውቀት፣ ስልጠና፣ የምርመራ አገልግሎት፣ የዲጂታል ድጋፍ ጋር የተያያዙ አስተዋፅኦዎች ተቀናጅተው ዘላቂ አቅምን ለመገንባት መዋል እንዳለባቸው ተናግረዋል። ለአርሶ አደሮች እና በዕሴት ሰንሰለቱ ውስጥ ላሉ ተዋናዮች ልዩ ትኩረት መስጠት እንደሚገባ ገልጸዋል።
አረንጓዴ ዐሻራ በዓለም አቀፍ ደረጃ የኢትዮጵያን ስም ከፍ ያደረገ ነው
Jul 6, 2026 493
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 29/2018(ኢዜአ)፦ አረንጓዴ ዐሻራ በዓለም አቀፍ ደረጃ የኢትዮጵያን ስም ከፍ ያደረገ መሆኑን የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ሰላማዊት ዳዊት ገለጹ። የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አመራርና ሠራተኞች በአዲስ አበባ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ ጎተራ ማሳለጫ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ አከናውነዋል። የአገልግሎቱ ዋና ዳይሬክተር ሰላማዊት ዳዊት በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በሁሉም መስክ ተጨባጭ ሀገራዊ ለውጦች እንዲመዘገቡ መሰረት እየጣለ ነው። የተሸረሸሩ እና የተጎዱ አካባቢዎች መልሰው እንዲያገግሙ አስችሏል ያሉት ዋና ዳይሬክተሯ፤ በምግብ ራስን የመቻል ግቦችን በማሳካት ረገድ አዎንታዊ ውጤቶች እየተመዘገበበት ነው ብለዋል። አገልግሎቱ ባለፉት ዓመታት በመርሃ ግብሩ በንቃት መሳተፉን ጠቅሰው፤ በ2018 በጀት ዓመት በአረንጓዴ አሻራ እና በተለያዩ በጎ ፈቃድ አገልግሎቶች የዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያጎሉ ተግባራትን በሰፊው እንደሚያከናውን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የወሰደችው የአረንጓዴ ዐሻራ ተግባራዊ ምላሽ ስሟን በዓለም መድረክ ከፍ ማድረጉን አስረድተዋል። ከዚህም ባለፈ ስለ አፍሪካ የሚነሱ የተዛቡ ትርክቶችን በማስተካከል ከፍያለ አህጉራዊ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በአዲስ አበባ የቂርቆስ ክፍለ ከተማ የብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ብርሃኑ አበራ በበኩላቸው፤ አረንጓዴ ዐሻራ የደን ሽፋን እንዲጭምር ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። ሁሉም በየአካቢው ችግኞችን በመትከል ሀገራዊ ኃላፊነቱን አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት የፕላንኒንግ ዳይሬክተር መሳይ አበበ እንደገለጹት፤ ዛሬ የምንተክለው ችግኝ ለቀጣዩ ትውልድ ዋስትና ነው ያሉ ሲሆን፤ ችግኞችን መትከል ብቻ ሳይሆን ተንከባክቦ ለውጤት ማብቃት ከኛ ይጠበቃል ብለዋል። አሻራዬን በማኖሬ እኮራለሁ ያሉት የአገልግሎቱ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ዳይሬክተር ማስተዋል ገዳ፤ የምንተክለው ችግኝ ብቻ ሳይሆን ለቀጣዩ ትውልድ ተስፋን ጭምር ነው ሲሉ ተናግረዋል። በቀጣይም የአረንጓዴ ዐሻራ ዘላቂ ግቦች እንዲሳኩ የሚጠበቅብኝን እወጣለሁ ብለዋል።
ያለፉት ዓመታት የአረንጓዴ ዐሻራ ሥራዎች የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የላቀ አስተዋፅኦ አበርክተዋል
Jul 6, 2026 373
ወላይታ ሶዶ፤ ሰኔ 29/2018 (ኢዜአ)፡- ባለፉት ዓመታት በከተማዋ የተከናወኑ የአረንጓዴ ዐሻራ ሥራዎች የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የላቀ አስተዋፅኦ ማበርከታቸውን የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር አስታወቀ። በከተማ አስተዳደሩ የዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሐሳብ በጉሩሞ ላዲሳ ቀበሌ ተካሂዷል። በወቅቱም የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማርያም እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ ሥራዎች የማኅበረሰቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ያስቻሉ ናቸው። በመርሃ ግብሩ ከዚህ ቀደም የተከናወኑ ተግባራት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የላቀ አስተዋፅኦ ማበርከታቸውንም ገልጸዋል። መርሃ ግብሩ የመሬት ለምነት እንዲጠበቅና የውሃ አካላት አቅማቸው እንዲጨምር ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ጠቁመው፣ ይህም በግብርናው ዘርፍ ለውጥ እንዲመጣ በማድረግ ተጨባጭ ውጤት ማስገኘቱን አስታውቀዋል። ዘንድሮ በሚከናወነው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በከተማው የአካባቢውን ሥነ-ምህዳር የሚጠብቁና ለምግብ ዋስትና መረጋገጥ አበርክቶ ያላቸው ችግኞች በስፋት እንደሚተከሉ ተናግረዋል። በዚህም ለደን፣ ለጥላ፣ ለውበት፣ ለኢኮኖሚ ምንጭነት የሚውሉ እንደ ቡና፣ ፍራፍሬ እና ሌሎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ላላቸው የችግኝ ዓይነቶች ትኩረት በመስጠት የመትከል ሥራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በሕዝቡ ዘንድ እየዳበረ የመጣው ችግኝ የመትከል ባህል እየተጠናከረ መምጣቱን ጠቁመው፣ የተተከሉትን ችግኞች በመጠበቅና በመንከባከብ ለውጤት እንዲበቁ የሚደረገው የተቀናጀ ጥረት ይጠናከራል ብለዋል። የከተማው ግብርና መምሪያ ኃላፊ ንጋቱ ቡሹራ በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የቡና፣ የእንሰት፣ የፍራፍሬና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ መጀመሩን ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩም 4 ነጥብ 6 ሚሊየን ችግኞችን በመትከል 680 ሄክታር መሬት ለማልማት መታቀዱን አስታውቀዋል። ችግኝ መትከል ለአካባቢው ሥነ-ምህዳር መስተካከል የሚያበረክተውን አስተዋጽኦ በመገንዘብ በየዓመቱ ችግኝ እየተከሉ መሆኑን የሚናገሩት ደግሞ አርሶ አደር ካሳሁን ሎሃ እና አርሶ አደር ኢዮብ ሰማ ናቸው። ችግኝ መትከል ከጀመሩ ወዲህ የተራቆቱ አካባቢዎች ለምተው ምርት መስጠት በመጀመራቸው፣ የምግብ ዋስትናቸውን ከማረጋገጥ በተጨማሪ የደረሱ ፍራፍሬዎችን ሸጠው በኢኮኖሚ ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን ገልጸዋል። ይህንን ለማስቀጠልም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች ለመትከል ቤተሰቦቻቸውን በማስተባበር ለዘንድሮው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ወደ ሥራ መግባታቸውን አክለዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለአካባቢ ጥበቃና ለስነ-ምህዳር መታደስ የላቀ አስተዋፅኦ እያበረከተ ነው
Jul 5, 2026 919
አዲስ አበባ፤ሰኔ 28/ 2018 (ኢዜአ):-የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሀገሪቱን የደን ሽፋን በማሳደግ ለአካባቢ ጥበቃና ለስነ-ምህዳር መታደስ የላቀ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን የኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ለሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቋቋም፣ የደን ሽፋንን ለማሳደግና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችለውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተተገበረ ይገኛል፡፡ በዚህም ታላቅ ሀገራዊ ንቅናቄ እስከ አሁን ባሉት ዓመታት ከ48 ቢሊዮን በላይ የደን፣ የፍራፍሬና የጥላ ችግኞችን ማልማት ተችሏል፡፡ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሐሳብ በሀገር አቀፍ ደረጃ ስምንት ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ዕቅድ ተይዞ ወደ ትግበራ ተገብቷል፡፡ በዛሬው ዕለትም የአዲስ አበባ ከተማ የጽዳት አስተዳደር ኤጀንሲ በረጲ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ ቦታ ተብሎ በሚጠራው ስፍራ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካሒዷል፡፡ የኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ለሊሴ ነሜ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር አካባቢን ከብክለትና መራቆት የምንጠብቅበት አንዱ መንገድ ነው ብለዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት የተተገበረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሀገሪቱን የደን ሽፋን በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደጉን ገልጸዋል፡፡ ይህም ለዓለም የአየር ንብረት መጠበቅ በረከት እየሆነ መምጣቱን ተናግረው፤ የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ረገድም ሚና እያበረከተ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ የሀገሪቱን የደን ሽፋን በማሳደግ ለአካባቢ ጥበቃና ለስነ-ምህዳር መታደስ የላቀ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር ወንድሙ ሴታ በበኩላቸው፤ በረጲ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ ቦታ አካባቢ በአሁኑ ወቅት በተሰራ የመልሶ ልማት ስራ ከአደጋ ስጋት ወደ ሀብትነት እየተቀየረ መጥቷል ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ጽዳት አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ገዛኸኝ ዴሲሳ በበኩላቸው፤ የረጲ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ ቦታ በአሁኑ ወቅት በችግኝ እየተሸፈነ ይገኛል ብለዋል፡፡ በዚህም በአሁኑ ወቅት በመልሶ መጠቀም ወደ ሀብትነት እየተቀየረ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ ኢዜአ ያነጋገራቸው የመርሃ ግብሩ ተሳታፊዎች፤ አረንጓዴ አሻራ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ በየዓመቱ በንቃት እየተሳተፉ መሆናቸውን ገልጸው፤ ቀደም ሲል በአካባቢያቸው የነበሩ የቆሻሻ መጣያ መሬቶች አሁን ላይ መልሰው በማገገም በአረንጓዴ ተክሎች መሸፈናቸውን ተናግረዋል።
የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ ልዑካን በታሪካዊቷ ላሊበላ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሄዱ
Jul 4, 2026 583
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ ልዑካን ቡድን አባላት በታሪካዊቷ ላሊበላ ከተማ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሂደዋል። ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የሀገራት አምባሳደሮችና የዓለም አቀፍ ተቋማት መሪዎች፣ በዩኔስኮ በተመዘገበው የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ቅጥር ግቢ ነው የአረንጓዴ ዐሻራቸውን ያኖሩት። በታሪካዊቷ የላሊበላ ጉብኝት በማድረግ ላይ የሚገኘው የዲፕሎማቲክ ልዑክ፣ ትናንት የዓለም ድንቅ ቅርስ የሆነውን የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን ጎብኝተዋል። ከጉብኝታቸው በተጓዳኝም በዛሬው ዕለት በቅርስ መዳረሻው የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ቅጥር ግቢ ውስጥ የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር አካሂደዋል። የልዑካኑ የችግኝ ተከላ የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከቅርስና አካባቢ ጥበቃ ጋር በአርዓያነት ተሰናስሎ የሚሰራበት መሆኑን ዓለም አቀፋዊ የልማት አጀንዳ መሆኑ ተገልጿል። ጉብኝቱና የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብሩ የኢትዮጵያን ጥንታዊነት፣ አስደናቂ የኪነ-ሕንጻ ጥበብና የባህል ዕሴቶችን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ይበልጥ ለማስተዋወቅ ትልቅ አጋጣሚን ፈጥሯል። ጉብኝቱም ኢትዮጵያ ለቱሪስቶች አስተማማኝና ማራኪ መዳረሻ መሆኗን ለዓለም በመገለጥ የቱሪዝም ዘርፍ ለማነቃቃት ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ተገልጿል። የዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ተወካዮች በቅርስ ስፍራው ችግኝ መትከላቸው፣ የዓለም ቅርሶችን የመንከባከብና የአየር ንብረት ለውጥን በጋራ የመከላከል ዓለም አቀፋዊ ትብብር ማሳያ ተደርጎም ይወሰዳል። የዲፕሎማቶች ጉብኝትና የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ኢትዮጵያ ታሪካዊና ተፈጥሯዊ ፀጋዎችን በመጠቀም ለመልካም ገጽታ ግንባታና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ለምታደርገው ጥረት አጋዥ ሚና ይኖረዋል።
ኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ስትራቴጂካዊ ፕሮግራሞችን በመተግበር ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበች ነው -ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ(ዶ/ር)
Jul 4, 2026 1311
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27 /2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአካባቢና የአየር ንብረት ለውጥ ተግዳሮቶችን በመቋቋም ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ስትራቴጂያዊ ፖሊሲዎችንና ፕሮግራሞችን በውጤታማነት በመተግበር ተጨባጭ ውጤት እያመጣች መሆኑን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፅም አሰፋ (ዶ/ር) ገለፁ። ለመጪው ትውልድ ጽዱ፣ ጤናማና አረንጓዴ ሀገር ለማስረከብ የተጀመረው የ"ጽዱ ኢትዮጵያን ለትውልድ" ሦስተኛው ዙር ሀገር አቀፍ ንቅናቄ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በተገኙበት ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ(ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደተናገሩት ሦስተኛው ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ባለፉት ሁለት ዙሮች የተገኙ ውጤቶችን በማስፋት ለሀገሪቱ ዘላቂ ልማትና አካባቢ ጥበቃ ወሳኝ አቅም የሚፈጥር ነው። ንቅናቄው ለዜጎች ጤናማና ንጹህ አካባቢ ለመፍጠር እና ለመጪው ትውልድ ፅዱ ኢትዮጵያን ለማውረስ የጋራ ቁርጠኝነትን ማረጋገጫ ነው ብለዋል። የከተሞች መስፋፋት፣ የፕላስቲክ ቆሻሻ መጨመር፣ የአደገኛ ኬሚካሎችና ቆሻሻዎች ተገቢ አያያዝ እጥረት፣ የድምፅ ብክለት እና ሌሎች የአካባቢ ችግሮች የዜጎችን ጤና፣ የአካባቢን ደህንነትና የዘላቂ ልማት ጉዞአችንን እየተፈታተኑ እንደሚገኙም አብራርተዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት የአካባቢና የአየር ንብረት ለውጥ ተግዳሮቶችን በመቋቋም ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ በርካታ ስትራቴጂያዊ ፖሊሲዎችንና ፕሮግራሞችን እየተገበረ ይገኛል ብለዋል። የአስር ዓመት የልማት ዕቅድ፣ የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ፣ የአየር ንብረትን የሚቋቋም አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ፣ የንፁህ ኃይል ሽግግር፣ የከተማ ኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች፣ አንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ የፕላስቲክ ከረጢቶችን የሚከለክል ሕግ፣ እንዲሁም የነዳጅ ተሽከርካሪዎችን ከውጭ የማስገባት ክልከላ የዚህ ቁርጠኝነት ተጨባጭ ማሳያዎች መሆናቸውን አብራርተዋል። በመርሃ ግብሮቹ ትግበራም ተጨባጭ ውጤት መምጣቱን አንስተዋል። ሀገሪቱ ለአካባቢ ጥበቃና ለአየር ንብረት ለውጥ ችግሮች እየወሰደቻቸው ያሉ የመፍትሔ እርምጃዎችና ያላት ቁርጠኝነት በዓለም አቀፍና በአህጉር ደረጃ ያላትን ተሰሚነት ከፍ ያደረገ መሆኑንም ገልፀዋል። በተለይ የአየር ንብረት ለውጥን በዘላቂነት ለመከላከል እንደሀገር በየዓመቱ እየተተገበረ ያለው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ከፍተኛ ውጤት የተገኘበት ነው ብለዋል። በአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን መሪነት እየተተገበረ የሚገኘው የፅዱ ኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄ ንፁህና ጤናማ አካባቢ ለመፍጠር እየተከናወኑ ካሉ ዓበይት ተግባራት አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል። የአካባቢ ጥበቃ ተቋማዊ ሥራዎችን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግም የተለያዩ ህግጋት ወደ ተግባር መግባታቸውን ተናግረዋል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ለሊሴ ነሜ(ዶ/ር)፥ ባለፉት ሁለት ዙሮች የተካሄዱ የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄዎች ለአካባቢ ጥበቃ ውጤታማ ተግባራት የተከናወነባቸው መሆናቸውን ተናግረዋል። በመጀመሪያው ዙር ከ15 ሚሊየን በላይ በሁለተኛው ዙር ደግሞ ከ54 ሚሊየን በላይ ህዝብ በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን ዘዴዎች ተደራሽ በማድረግ በባለቤትነት እንዲሳተፉ መደረጉን አንስተዋል። 3ኛው ዙር ንቅናቄ የፕላስቲክ ብክለት፣ የአደገኛ ኬሚካሎችንና አደገኛ ቆሻሻዎችን መከላከል እንዲሁም የድምፅ ብክለትን መከላከል ላይ ያተኮረ መሆኑን ጠቅሰዋል። የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ለአካባቢ ጥበቃ መሰረት እየጣለ መሆኑን ገልጸው፥ ለስኬታማነቱ ጠንካራ የሕዝብ ተሳትፎና የጋራ ቁርጠኝነትን እንደሚጠይቅ አስረድተዋል።
የአካባቢ ብክለትን መከላከል ከሀገሪቱ የወደፊት እጣ ፈንታ ጋር የተሳሰረ ብሔራዊ የልማትና ደኅንነት ጉዳይ ነው
Jul 4, 2026 1238
የአካባቢ ብክለትን መከላከል ከሀገሪቱ የወደፊት እጣ ፈንታ ጋር የተሳሰረ ብሔራዊ የልማትና ደኅንነት ጉዳይ ነው አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የአካባቢ ብክለትን መከላከልና የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ከኢኮኖሚ ምርታማነትና ከሀገሪቱ የወደፊት እጣ ፈንታ ጋር የተሳሰሩ ብሔራዊ የልማትና ደኅንነት ጉዳዮች መሆናቸውን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለፁ። ኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃና በአረንጓዴ ልማት ለአፍሪካ ተምሳሌት ሀገር መሆን መቻሏንም ገልጸዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ 3ኛውን ዙር የ"ጽዱ ኢትዮጵያን ለትውልድ" ሀገር አቀፍ ንቅናቄ በይፋ አስጀምረዋል። በዚህ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክትም፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በመላ ሀገሪቱ በመደመር መንግሥት እየተተገበረ ያለው የኮሪደር ልማትና የወንዝ ዳርቻ ልማት ከተሞችን ጽዱ፣ አረንጓዴ፣ ውብ እንዲሁም ለነዋሪዎች ምቹ ከማድረጉም ባሻገር፣ የቱሪስት መስሕብነታቸውን እያሳደገው መሆኑን ተናግረዋል። ሦስተኛው ዙር የጽዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄም ከእነዚህ ሀገራዊ መርሃ ግብሮች ጋር በተቀናጀ መልኩ እንደሚተገበር ገልጸዋል። የፕላስቲክ ብክለት፣ የአደገኛ ቆሻሻዎች አያያዝ እና የድምፅ ብክለት ለአካባቢ ጥበቃ ጉዳዮች ብቻ ሳይሆኑ ከሕዝብ ጤና፣ ከኢኮኖሚ ምርታማነት፣ ከኢንቨስትመንትና ከሀገሪቱ የወደፊት እጣ ፈንታ ጋር የተሳሰሩ ብሔራዊ የልማትና ደኅንነት ጉዳዮች መሆናቸውን አስገንዝበዋል። እነዚህን ተግዳሮቶች መፍታት የአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፣ የሀገራችንን ዘላቂ ልማት፣ ተወዳዳሪነት እና የትውልዶችን የወደፊት ዕድል የሚወስን ሀገራዊ ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነውም ብለዋል። ባለፉት ሁለት ዙሮች የተካሄዱት የጽዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄዎች በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች የተሳተፉባቸውና ትልልቅ ስኬቶች የተመዘገቡባቸው መሆኑን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። ሦስተኛው ዙር ንቅናቄም የቀደሙትን ጠንካራ ጎኖች በማጠናከር እንዲሁም የክትትል፣ የሪፖርት ሥርዓት እና የተቋማዊ ቅንጅት ክፍተቶችን በጥልቀት በመገምገም መዘጋጀቱን አስረድተዋል። ንቅናቄው በግንዛቤ ፈጠራ ላይ ብቻ ሳይወሰን በሚለኩ ውጤቶች፣ በጠንካራ ክትትልና ግምገማ እንዲሁም በተቋማዊ ተጠያቂነት ላይ በትኩረት እንደሚሠራ አስታውቀዋል። የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን በብክለት መከላከል፣ በአካባቢ ጥበቃና ተያያዥነት ባላቸው ሕጎች ዝርጋታና ተፈጻሚነት እንዲሁም በኅብረተሰብ ግንዛቤ ፈጠራ ላይ ተምሳሌታዊ ሥራዎችን እያከናወነ ይገኛል ብለዋል። የንቅናቄውን ስኬታማነት ለማረጋገጥ ሁሉም የክልል መንግሥታትና የከተማ አስተዳደሮች እንደየአካባቢያቸው ሁኔታ ግልጽ የትግበራ ዕቅድ በማዘጋጀት፣ በጀት በመመደብና ጠንካራ የክትትልና ሪፖርት ሥርዓት በመዘርጋት መስራት እንደሚጠበቅባቸውም አሳስበዋል። በተለይም የክልል ፕሬዚዳንቶች፣ ከንቲባዎችና የአካባቢ ጥበቃ ተቋማት አመራሮች የመሪነት ኃላፊነታቸውን በብቃት እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። ለሀገራዊ ንቅናቄው መሳካት የግሉ ዘርፍ፣ የሲቪል ማኅበራት፣ የሃይማኖት ተቋማት፣ ሴቶችና ወጣቶች በአንድነት እንዲንቀሳቀሱም ጠይቀዋል። መጪው ትውልድ የሚረከባት ኢትዮጵያ ከሙስና፣ ከአድልዎና ከብልሹ አሠራር ብሎም ከአካባቢ ብክለት የጸዳች እንድትሆን የጋራ ቁርጠኝነት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። የተጀመረው ጉዞ ለጽዱ አካባቢ፣ ለጤናማ ማኅበረሰብ፣ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ እና ለተሻለች ኢትዮጵያ የሚደረግ የጋራ ጉዞ ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ለመጪው ትውልድ የምናስተላልፈው ትልቁ ቅርስ ጽዱ፣ አረንጓዴ፣ ጤናማ እና ዘላቂ ኢትዮጵያ መሆን አለበት ብለዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐግብር የአደጋ ቅድመ መከላከል ውጤታማነትን እያጎለበተ ነው
Jul 4, 2026 339
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከተሞችን ውበት በማጎናጸፍ የአደጋ ቅድመ መከላከል ውጤታማነትን እያጎለበተ መሆኑን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር ወንድሙ ሴታ ገለጹ። የአዲስ አበባ የእሳትና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አመራር፣ ሠራተኞችና ባለድርሻ አካላት በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል አካባቢ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሂደዋል። በመርሃ ግብሩ የተገኙት በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ወንድሙ ሴታ፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ቢሊዮን ችግኞችን መትከል ያስቻለ ስኬታማ የልማት ንቅናቄ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ህዝቦቿን በማስተባበር በየዓመቱ በብሔራዊ የአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄ የምትተክላቸው ችግኞች የአካባቢ ጥበቃን በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የጎርፍ፣ መሬት መንሸራተትና የአፈር መሸርሸርን በመቀነስ ለአደጋ ቅድመ መከላከል ውጤታማነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የአረንጓዴ ልማት ተምሳሌት ከተሞችን በማስፋፋትም ንጹህ አየርና ውብ ገጽታ የተላበሰ ምኅዳር እንዲፈጠር በማድረግም ጉልህ ፋይዳ እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከተሞችን ውበት በማጎናጸፍ የአደጋ ቅድመ መከላከል ውጤታማነትን እያጎለበተ ነውም ብለዋል፡፡ አዲስ አበባም የአረንጓዴ ውበት ምሳሌ ሆናለች ያሉት ኢንጂነር ወንድሙ፤ በቀጣይም ማህበረሰቡ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተለመደውን ንቁ ተሳትፎ ማድረግ እንዳለበት ጥሪ አቅርበዋል። የአዲስ አበባ የእሳትና አደጋ ስጋት ሥራ አመራር ኮሚሽነር አሕመድ መሐመድ በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የአካባቢ ልማት ብቻ ሳይሆን የቅድመ አደጋ መከላከል ሥራ ነው ብለዋል። በዚህም ባለድርሻ አካላት በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ችግኞችን በመትከልና በመንከባከብ የጎርፍና ተያያዥ አደጋዎችን ቀድሞ መከላከል እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።
ከብክለት ወደ ውበት፡ የቀበና ወንዝ አዲስ ገጽታ
Jul 3, 2026 461
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የእንጦጦ - ቀበና የወንዝና የወንዝ ዳርቻ ልማት እንዲሁም የቀበና ግድብ ፕሮጀክትን ሰኔ 21 ቀን 2018 ዓ.ም መርቀው ለአገልግሎት ክፍት ማድረጋቸው ይታወሳል። አንድን ከተማ ህያውና ለነዋሪዎቿ ምቹ የሚያደርጓት ዋና ዋና መገለጫዎች የተፈጥሮ አካባቢዎቿ፣ ወንዞቿና አረንጓዴ ስፍራዎቿ ናቸው። ይሁን እንጂ ለረጅም ዘመናት የአዲስ አበባ ወንዞችና ዳርቻዎቻቸው የውበት ምንጭ መሆናቸው ቀርቶ የቆሻሻ መጣያና የብክለት ማዕከል ሆነው መቆየታቸው የቅርብ ጊዜ ትውስታ ነው። ዛሬ ላይ ግን ይህ ታሪክ እየተቀየረ፣ የከተማዋን ገጽታ ሙሉ በሙሉ የሚቀይሩ አስደናቂ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ የሚገኙ ሲሆን ከእነዚህም መካከል በአጭር ጊዜ ውስጥ ከፍተኛ ለውጥ በማምጣት ለከተማዋ ተጨማሪ ድምቀትና ውበት የፈጠረው የቀበና ወንዝ ዳርቻ ልማት አንዱና ዋናው ማሳያ ነው። ይህ በአሁኑ ወቅት የአይን ማረፊያ የሆነው ስፍራ ቀደም ሲል የነበረው ገጽታ እጅግ አስከፊ ነበር። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የከተማዋ ነዋሪዎች እንደሚገልጹት፤ ቀደም ሲል ከአካባቢው ማህበረሰብና ከተለያዩ አቅጣጫዎች በሚለቀቁ ቆሻሻዎች ሳቢያ በወንዙ ውስጥ ይፈስ የነበረው ውሃ በከፍተኛ ሁኔታ የተበከለ ነበር። ስፍራው በአይን ለማየት እንኳን እስከማይመች ድረስ የተበላሸና ለአካባቢው ነዋሪዎችም ትልቅ የጤናና የደህንነት ስጋት ደቅኖ የኖረ መሆኑን ያስታውሳሉ። ሆኖም ግን፣ ለአካባቢው አዲስ ገጽታን ያላበሰው ይህ የልማት ስራ ማህበረሰቡን በእጅጉ አስደስቷል። ወደ መልካም ገጽታ የተለወጠው ይኸው የተፈጥሮ አካባቢ፣ ነዋሪዎች ምቹና ጤናማ መኖሪያ እንዲያገኙ የተደረገውን ጥረት ስኬታማነት በግልጽ ያሳያል። አስተያየታቸውን ከሰጡት የአከባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ ገዛኸኝ ደሩ እንዳሉት የቀበና ወንዝ እና አካባቢው ቀደም ሲል ለኑሮ የማይመች፣ በቆሻሻና በመጥፎ ጠረን የሚታወቅ ነበር። በአካባቢው ነዋሪዎች ላይ ከፍተኛ የጤና እና የደህንነት ስጋት ደቅኖ የነበረውና ቆሻሻ መጣያ የነበረው ገደላማ ስፍራ፣ በአሁኑ ወቅት በአመርቂ ሁኔታ ጽድቶና ለምቶ ማየት ችለናል ብለዋል። ይህንን ማህበራዊና አካባቢያዊ ችግር ለመቅረፍ በተከናወኑ የልማትና የጽዳት ስራዎች፣ ስፍራው በአሁኑ ወቅት ውብና ለዓይን የሚማርክ እይታን መጎናጸፍ መቻሉን ጠቅሰዋል። ወይዘሮ እታፈራው መንግስቱ በበኩላቸው የቀበና ወንዝ ለረጅም ዘመናት ተበክሎ የቆየ ቢሆንም፣ አሁን የተከናወነው የልማት ስራ ግን ትልቅ ለውጥ አምጥቷል። በተለይም በወንዙ ላይ ግድብ መሰራቱ ይበልጥ ውብ እንዲሆን ከማድረጉም በላይ፣ በአሁኑ ወቅት በእግር ለመጓዝ ምቹ መሆኑንም ጠቅሰው ቀደም ሲል የነበረው አስከፊ ገጽታ አሁን ላይ ሙሉ በሙሉ ተቀይሮ በማየቴ ታላቅ ደስታ ተሰምቶኛል ብለዋል፡፡ የቀበና ወንዝ ዳርቻ ልማት የወንዞችን ብክለት ከመቀነስ ባለፈ፣ የከተማን ገጽታ እንዴት በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ላቀ የውበት ደረጃ ማሸጋገር እንደሚቻል የታየበት ትልቅ ስኬት ነው። ቀደም ሲል ከአካባቢው ማህበረሰብና ከተለያዩ አቅጣጫዎች በሚለቀቁ ቆሻሻዎችና በሚወጣው መጥፎ ጠረን ሳቢያ ወንዙ በከፍተኛ ሁኔታ የተበከለ ነበር ብለዋል። አቶ በየነ ድልነሳው እና አቶ ደረጄ በሰጡት አስተያየትም፤ ስፍራው በአይን ለማየት እንኳን እስከማይመች ድረስ የተበላሸ፣ ማህበረሰቡን ለተለያዩ የጤና እክሎችና ለደህንነት ስጋት ይዳርግ የነበረ የጤና ጠንቅ እንደነበር ያስታውሳሉ። ይሁን እንጂ ይህንን ማህበራዊና አካባቢያዊ ችግር ለመቅረፍ በተከናወኑ የልማትና የጽዳት ስራዎች፣ በአሁኑ ወቅት በአካባቢው ላይ አመርቂ ለውጥ መምጣቱን ነዋሪዎቹ ይመሰክራሉ። አሁን ላይ አካባቢው ትልቅ ለውጥ በማሳየት፣ ለነዋሪዎች ማራኪ የመኖሪያ ስፍራ ከመሆኑም በላይ ለህጻናትና ለአዋቂዎች ጭምር ታላቅ አማራጭ ምቹ የመዝናኛ ስፍራ መሆኑን የጠቆመው ደግሞ ወጣት አሸናፊ ነው፡፡ ይህ ፕሮጀክት የአካባቢውን ማህበራዊና የጤና ስጋቶች ሙሉ በሙሉ በመቅረፍ፣ በተገቢው እቅድና ቁርጠኝነት ከተሰራ የተበከሉ የተፈጥሮ ሃብቶቻችንን መልሶ ማልማትና ለከተማ ውበት ማዋል እንደሚቻል ትልቅ ማሳያ ሆኗል። ፕሮጀክቱ ለአካባቢው ማህበረሰብ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለውሲሆን የተገኘውን ውበት ዘላቂ ለማድረግ ትልቅ አደራና የቤት ስራ መውሰድ እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡ ይህ ግዙፍ ፕሮጀክት ትውልድ ተሻጋሪ እንዲሆንና ለረጅም ዓመታት አገልግሎት መስጠት እንዲችል ሁላችንም በባለቤትነት ስሜት ልንጠብቀውና ልንንከባከበው ይገባል ሲሉም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። የለማውን ውበት ይዞ ለመቀጠል ማህበረሰቡ አካባቢውን በመንከባከብ ረገድ የዜግነት ድርሻውን ሊወጣ ይገባል ብለዋል። 87 ነጥብ 6 ሄክታር መሬት የሚሸፍነውን እና 10 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ፕሮጀክቱ ከተማዋን ጽዱ ከማድረግ ባለፈ ለነዋሪዎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው ሆኗል።
ዘላቂ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጠው የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ
Jul 3, 2026 400
በዮሐንስ ደርበው ዐቅምን በመሰብሰብ በመደመር ዕሳቤ እየተከናወነ ያለው የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ጥቅም ንጥልም ቀላልም አይደለም፤ በተለያዩ ዐውዶች ገዝፎ ይገለጣል እንጂ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ አረንጓዴ ዐሻራ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ብልጽግናን አሠናሥሎ የሚያረጋግጥ ብሔራዊ ኢኒሼቲቭ ነው። የደን፣ የሰብልና ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ወሳኝ የልማት አቅጣጫም ነው። ከችግኝ ተከላ የላቀው የአረጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ መነሻ፤ የተራቆተ አካባቢን ችግኝ በመትከል አረንጓዴ ከማድረግ የላቀ ድርብርብ ግብ ያለው ሰፊ መርሐ-ግብር ነው። በዚህም መሠረት፤ እንደየ ሥነ-ምኅዳሩ የሚላመዱ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ላላቸው ችግኞች፣ ለደን ሽፋን ማደግ የጎላ ሚና ለሚኖራቸው ችግኞች፣ ለከተማ ውበትና ለማረፊያ ጥላ ለሚሆኑ ዛፎች፣ መሬትን ቆንጥጦ በመያዝ የአፈር መሸርሸርን ለመከላከል የሚችሉ ዛፎች የሚተከሉበት ነው። ይህም አንድን አካባቢ አረንጓዴ ከማድረግ ልቆ በረሃማነትን በመቀነስ፣ የዓየር ንብረት ተጽዕኖን በመቀነስ፣ ምርታማነትን በመጨመር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያሳድግ ነው። የአካባቢ መጎዳት የሚያስከትለው ቀውስና የተፈጥሮ አደጋ በመላው ዓለም በስፋት እየታየ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጭነትና ቁርጠኛ አመራር ሰጭነት ባለፉት ዓመታት በብርቱዎቹ ኢትዮጵያውያን ርብርብ ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞች ተተክለዋል፤ ውጤቱንም ሕዝቡ ዐይቷል። ከውጤቶቹ መከካልም ለአብነት፤ ከሀገራዊ ለውጡ በፊት 17 ነጥብ 2 በመቶ የነበረው የደን ሽፋን አሁን ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ማደጉ፣ የምርታማነትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት መጨመር ብሎም ውብና አረንጓዴ ከተሞች መስፋፋት የሚሉት ይነሳሉ። በሕዝቡ ዘንድ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ተፈጥሮን የመንከባከብ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፤ የሀገርን የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትና የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ጉዳይ ጭምር ተደርጎ መወሰድ ይኖርበታል። የአረንጓዴ ዐሻራን ውጤት ላጣጣመ ሥራውን በንቃት እንዲከውን መካሪ ባያሻም፤ ካለፈው የበለጠ ውጤት እንዲገኝ ዛሬ ላይ ኢትዮጵያውያን በነቂስ መሳተፍ ባህል እያደረጉት ይገኛል። ከአረንጓዴ ዐሻራ ትሩፋቶች መካከል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጭነት በ2011 ዓ.ም ጅማሮውን ያደረገው የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ አሁን ዘርፈ-ብዙ ጥቅሙ በተጨባጭ እየተገለጠ ነው። ከበርካታ ትሩፋቶቹ መካከልም የምርታማነት ማደግ ተጠቃሽ ነው። ይህን ተከትሎም የሕብረተሰቡ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት አድጓል። ይህን ሐሳብ በአኃዝ አስደግፈን ብናየው፤ ከአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ በፊት (በ2010 ዓ.ም) በሔክታር የሚመረተው ስንዴ 22 ኩንታል፣ በቆሎ 30 ኩንታል፣ ጤፍ 17 ኩንታል እንዲሁም ገብስ 23 ኩንታል ነበር። ከኢንሼቲቩ ትግበራ በኋላ ደግሞ (በ2017 ዓ.ም) ስንዴ በሔክታር 36 ኩንታል፣ በቆሎ 46 ኩንታል፣ ጤፍ 20 ኩንታል፣ ገብስ 30 ኩንታል ማምረት ተችሏል። በዚህም መሠረት በ2017 ዓ.ም 7 ነጥብ 8 ሚሊየን ሔክታር መሬት በስንዴ ሰብል በመሸፈን 280 ሚሊየን ኩንታል ማምረት ተችሏል። ስንዴን በትጋት በማምረትም ከውጭ ለማስገባት ይወጣ የነበረን 1 ቢሊየን ዶላር የውጭ ምንዛሬ ማስቀረት ተችሏል። በሌላ በኩል ደግሞ፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ በፍራፍሬው ዘርፍ ዕድገትም ከፍተኛ አስተዋጽዖ አበርክቷል። በዚህም ገበያውን ከማረጋጋት ባለፈ ሕብረተሰቡ (አምራቹ) ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱ በዚያው ልክ እንዲያድግ አስችሏል። ኢትዮጵያም በአፍሪካ አቮካዶን በቀዳሚነት ወደ ውጭ የምትልክ ሁለተኛዋ ሀገር እንድትሆንም አስችሏታል። ሌላኛው የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ትሩፋት የቡና ልማት መስፋፋትና የውጭ ምንዛሬ ማደግ ነው። ይህን በአሥረጂ አስደግፈን ብንመለከት፤ በ2011 ዓ.ም በ600 ሺህ ሔክታር ላይ ቡና ተተክሏል። 500 ሺህ ሜትሪክ ቶን የቡና ምርት ተሰብስቧል። 738 ሚሊየን የአሜሪካ ዶላር ገቢ ተገኝቷል። እንዲሁም በ2017 ዓ.ም 1 ነጥብ 4 ሚሊየን ሔክታር መሬት ላይ ቡና ተተክሏል። 1 ነጥብ 58 ሚሊየን ሜትሪክ ቶን የቡና ምርት ተሰብስቧል። 2 ነጥብ 65 ቢሊየን የአሜሪካ ዶላር ገቢም ማግኘት ተችሏል። በ2018 የበጀት ዓመት ደግሞ ወደ ውጪ ከተላከ የቡና ምርት 3 ቢሊየን ዶላር ገቢ ተገኝቷል። እንዲሁም ከአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ጋር በተያያዘ ለ2 ነጥብ 5 ሚሊየን ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል። የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ፤ የአካባቢ መራቆትን በመቀነስና በመቅረፍ ከፍተኛ አስተዋጽዖ አበርክቷል፣ በደን መጨፍጨፍ ምክንያት ይከሰት የነበረን የበረሃማነት መስፋፋት ቀንሷል፣ የደን ሽፋንን ጨምሯል፣ የአፈር መሸርሸርን በመቀነስ መሬት እንዲያገግም በማድረግ ምርታማነትን ጨምሯል። በተጨማሪም የውኃማ አካላትን መመናመን ቀንሷል (ደርቀው የነበሩ ስፍራዎች ወደ ቀድሞ ውኃማ ይዘታቸው እንዲመለሱ አስችሏል)፣ የአካባቢ መራቆትና የዓየር ንብረት ፈተናዎችን በመቀነስ ረገድም የራሱን ከፍተኛ ሚና አበርክቷል። ከአረንጓዴ ዐሻራ ጋር በተያያዘ በቀጣይ የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ የለውጡ መንግሥት ከመጣ ወዲህ ላለፉት ዓመታት በተቀናጀ አግባብ ተመርቷል፤ አሁንም እየተተገበረ ነው። በቀጣይ ደግሞ ኢኒሼቲቩ እንዴት መከናወን እንዳለበት ግቦች ተቀምጠዋል። በዚህም መሠረት፤ የሕዝብ ባለቤትነትን አጠናክሮ ማስቀጠል (አረንጓዴ ባሕል መገንባት)፣ አማራጭ የኃይል አቅርቦት ሥራዎችን ማስፋትና በደን ላይ የሚደርሰውን ጫና መቀነስ፣ የሕግና የፖሊሲ ማሻሻያ የሚፈልጉ ጉዳዮችን ለይቶ በጥናት መመለስ የሚሉት የቀጣይ አቅጣጫዎች ናቸው። በተጨማሪም፤ ከአረንጓዴ ዐሻራ የሚገኘውን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት አጠናክሮ ማስቀጠል፣ የባለድርሻ አካላት እና የተቋማት ቅንጅታዊ አሠራርን ማጠናከር፣ በክረምት ወራት የሚተከሉ ችግኞችን በበጋ ወራት በአግባቡ መንከባከብ ከቀጣይ አቅጣጫዎች መካከል ናቸው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሐሳብ በቢሾፍቱ ማስጀመራቸው ይታወቃል። ከ8 ቢሊየን በላይ ችግኞች ለተከላ ዝግጁ በሆኑበት በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ ወቅት አረንጓዴ ለሆነች ነገ፣ ሁላችንም ተስፋን እንትከል ሲሉ ለሀገሬው ጥሪ አቅርበዋል። ከላይ የተጠቀሱ ማሳያዎችን (ናሙናዎችን) ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ በቀጥታ ለሕዝቡ ጥቅም የቆመ ሰው ተኮር መርሐ-ግብር መሆኑን መገንዘብ አያዳግትም። ስለዚህ በቀጣይ ሕብረተሰቡ በመደመር ዕሳቤ በዚህ ኢኒሼቲቭ ላይ ያለጠባቂነት በንቃት የመሳተፍ ልምዱን ማሳደግ አለበት
በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ62 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ይተከላሉ
Jul 3, 2026 302
ወላይታ ሶዶ፤ ሰኔ 26/2018(ኢዜአ)፦በወላይታ ዞን በዘንድሮው ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ62 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እንደሚተከሉ የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለጸ። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ ዘማች ሶርሳ (ዶ/ር) እንደገለፁት፤"ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሃሳብ በተጀመረው የዘንድሮው የክረምት ወራት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከ62 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ይተከላሉ። እንዲሁም በመርሃ ግብሩ ከ105 ሚሊዮን በላይ የፍራፍሬ፣ የቡና እና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል። በዞኑ መርሃ ግብሩ የመሬት ለምነትን በመመለስና የጠፉ ምንጮች እንዲፈልቁ በማድረግ ረገድ ዘርፈ ብዙ ትሩፋቶችን ማስገኘቱን የጠቀሱት ኃላፊው፣ ይህንን አጠናክሮ ለማስቀጠል በተቀናጀ መልኩ እየተሰራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በዚህም ሁሉም የዞኑ ማህበረሰብ በችግኝ ተከላና እንክብካቤ ላይ ያለውን ተሳትፎ በማጠናከርና አሻራውን በማሳረፍ፣ ለነገው ትውልድ ውብና ለምለም አካባቢን የማስረከብ ትልምን ለማሳካት የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣም አሳስበዋል። በዞኑ በጠበላ ከተማ የአላታ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አለሙ ኦሳ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ የአካባቢያቸው ስነ-ምህዳር መሻሻሉን ገልጸዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተገኘውን ዘርፈ ብዙ ለውጥ አጠናክሮ ለማስቀጠል በንቃት እየተሳተፉ መሆናቸውን ጠቅሰው፣ አሁን ላይ ችግኞችን መትከልና መንከባከብን ባህል አድርገው እየከወኑት እንደሚገኙ ተናግረዋል። "ችግኝ መትከል ከጀመርን ወዲህ የማሳችን ልምላሜ እንዲሁም ምርትና ምርታማነታችን ጨምሯል" ያሉት አርሶ አደሩ፣ ዘንድሮም ይህንን ለውጥ ለማስቀጠል የቡና፣ የፍራፍሬ እና ሌሎችንም ችግኞችን በስፋት እየተከሉ መሆናቸውን አስረድተዋል። በዞኑ በሁምቦ ወረዳ የሾጮራ ኦጎዳማ ቀበሌ አርሶ አደር ሳፈነ ሻንካ እና በለጠ በርገነ በበኩላቸው፣ ከዚህ ቀደም በቂ ግንዛቤ ባለመኖሩ ዛፎችን በብዛት በመቁረጣቸው አካባቢያቸው ተራቁቶ በድርቅና በረሃብ ሲጎዱ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። መርሃ ግብሩ ከተጀመረ ወዲህ ግን ለምግብነት፣ ለገበያ የሚሆኑና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች በመትከላቸው ስነ-ምህዳሩ ተሻሽሎ ዝናብ በወቅቱ እያገኙ መሆኑን ጠቅሰው፤ ጠፍተው የነበሩ ምንጮች እየፈለቁና ለእንስሳትም በቂ መኖ ማግኘት መጀመራቸውን አንስተዋል። በመሆኑም የተገኘውን ለውጥ ለማስቀጠል በተከላውም ሆነ በእንክብካቤው ስራ ላይ ሳንታክት እንሰራለን ብለዋል።
በአረንጓዴ አሻራ ቋሚ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ በመሆን ሕይወታችንን በመለወጥ ላይ እንገኛለን
Jul 3, 2026 309
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 26/2018 (ኢዜአ)፡- በአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር ቋሚ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ በመሆን ሕይወታችንን በመቀየር ላይ እንገኛለን ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው ሴቶች ገለጹ፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም. በተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ባለፉት ዓመታት ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ታሪካዊ እና አስደማሚ አሻራ ማኖር ተችሏል፡፡ በተያዘው ዓመትም 8 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ወደ ትግበራ ተገብቷል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ደረጃም ባለፉት ሰባት ዓመታት 90 ሚሊዮን ችግኞችን በመትከል የአረንጓዴ ሽፋኑን እጅግ ዝቅተኛ ከነበረበት 2 ነጥብ 8 በመቶ ወደ 24 በመቶ ማድረስ ተችሏል ። በአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብር የተራቆቱ አካባቢዎች አረንጓዴ ለብሰዋል፤ የነጠፉ ወንዞች እና አካባቢዎች ማንሰራራት የቻሉ ሲሆን አዲስ አበባን ንፁህ፣ ውብ፣ ለመኖር ምቹ እና የቱሪስት ማዕከል መሆን ችላለች። በዚህ ዓመት በከተማ ደረጃ ስድስት ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል የማስመጀሪያ መርሐ ግብር ተከናውኖ የተከላ ሂደት ተጀምሯል፡፡ በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች ችግኝ በማፍላት ሥራ ላይ የተሰማሩ ዜጎች በመርኃ-ግብሩ የሥራ ዕድል ተጠቃሚ በመሆን ኑሯቸውን በማሻሻል ላይ ይገኛሉ፡፡ በችግኝ ማፍላት ሥራ ላይ የተሰማራችው አበበች ተካ፣ ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚውሉ ችግኞችን በማፍላትና በማቅረብ ቋሚ ሥራና አስተማማኝ ገቢ በማግኘት ላይ መሆኗን ጠቅሳለች፡፡ በዚህም ኑሮዋን በበጎ ሁኔታ በመምራት ላይ እንደምትገኝ ገልጻለች። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ራሔል ዮሐንስ በበኩሏ፤ በችግኝ ጣቢያ ውስጥ ያገኘችው ሥራ ገቢ አግኝታ ከኢኮኖሚ ጥገኝነት እንድትላቀቅና ከራሷ አልፋ ቤተሰቦቿን መደገፍ እንድትችል ማድረጉን ጠቅሳለች፡፡ ችግኞችን መንከባከብ ለአካላዊና መንፈሳዊ ጤንነቷ ከፍተኛ አዎንታዊ ስሜት እንደሚፈጥርላት ተናግራለች። ለበርካታ ዓመታት በአረብ ሀገር በስደት ቆይታ ወደ ሀገሯ የተመለሰችው ሐና ማሞ እንዳለችውም፤ በሀገር ላይ ሠርቶ ከመለወጥ የበለጠ ደስታና ዓለም እንደሌለ ትናገራለች። ወደ ሀገሯ በመመለስ በተፈጠረላት የሥራ ዕድል በቋሚነት ችግኝ በማፍላትና በማቅረብ ሥራ ላይ መሰማራቷን ጠቅሳ፤ ሀገርን የሚጠቅም ሥራ እየሠራች ራሷም ተጠቃሚ መሆን መቻሏ ልዩ ደስታ እንደፈጠረላት አመልክታለች። በዚህም በችግኝ ጣቢያ ማዕከል ውስጥ ሥራ በመሥራት ራሷንና ቤተሰቧን በመደገፍ ኑሮዋን በበጎ ሁኔታ በመመስረት ላይ መሆኗን ገልጻለች። የከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ የአረንጓዴ ቦታዎች አያያዝ፣ ክትትልና ቁጥጥር ዳይሬክተር አቶ ሲሳይ አጥናፉ ፤ በዘንድሮው የክረምት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ላይ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸው ከፍተኛ የሆኑ በርካታ የፍራፍሬና ሌሎች ሀገር በቀል ዝርያ ያላቸው ችግኞች በስፋት መዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል። ቢሮው በችግኝ ማፍላት ሥራ ላይ ብቻ ከአራት መቶ በላይ ለሚሆኑ ወጣቶችና ሴቶች ቋሚ የሥራ ዕድል መፍጠሩን ጠቁመዋል፡፡
አረንጓዴ ዐሻራ የሥርዓተ ምህዳር ደህንነትን በማስተካከል ለዱር እንስሳት ሀብት ጥበቃ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Jul 3, 2026 560
አዲስ አበባ ፤ሰኔ 26/2018 (ኢዜአ)፦አረንጓዴ ዐሻራ የአካባቢ ሥርዓተ ምህዳር ደህንነትን በማስተካከል ለዱር እንስሳት ሀብት ጥበቃ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጂራ ገለጹ። ኢትዮጵያ ባለፉት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብሮች ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን ተክላለች። በዚህም የአገሪቱ የደን ሽፋን ከ17 ነጥብ 2 በመቶ ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ብሏል። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጂራ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ለዱር እንስሳት ሀብቶች መጠበቅ ያበረከተውን አስተዋጽኦ በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የዱር እንስሳት ሀብቶቻችንን ጠብቆ ለማቆየት ምቹ አካባቢን መፍጠር ይገባናል ብለዋል። ልዩ ልዩ የዱር እንስሳት ተገቢውን ጥበቃ እንዲያገኙ የሚኖሩበትን የደን ስፍራ ከተለያዩ የተፈጥሮ አደጋዎች መከላከል ተገቢ መሆኑን አንስተዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር መተግበር ከጀመረ ወዲህ የተራቆቱ መሬቶችን ወደ ተፈጥሯዊ ሥነ ምህዳር በመመለስ ረገድ ከፍተኛ ሚና መጫወቱን በመግለጽ፤ ይህም ለዱር እንስሳት ተስማሚ የአካባቢ ሥርዓተ ምህዳር ፈጥሯል ብለዋል። በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የእጽዋት ሽፋን በጨመረባቸው አካባቢዎች፤ የአእዋፋት እና የዱር እንስሳት ቁጥር እየተበራከተ መምጣቱን አክለዋል። ለአብነትም በአቢጃታ-ሻላ ሐይቆች ብሔራዊ ፓርክ የቆላ አጋዘንን ጨምሮ ሌሎች የዱር እንስሳትን በስፋት ማየት የተቻለበት ሁኔታ መኖሩን ተናግረዋል። ቀደም ሲል የሐይቁ መጠን በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱን አስታውሰው፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ትግበራ የሐይቁን የውኃና የመልክዓ ምድር ስፋት እንዲጨምር ማድረጉንና አእዋፋት በስፋት የሚታዩበትን ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል። በተመሳሳይ ሁኔታ የሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ በተደጋጋሚ የደን ቃጠሎ የሚታይበት እንደነበረ አስታውሰው፤ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር መጀመሩ ጉዳቱን ለመቀነስ ትልቅ አቅም መፍጠሩን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ሰኔ 8 ቀን 2018 ዓ.ም በቢሾፍቱ ከተማ ማስጀመራቸው ይታወቃል። በዚህም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው 8 ቢሊዮን ችግኞችን የመትከል ግብ ተይዞ እየተሠራ ይገኛል።
አረንጓዴ አሻራ ለከተሞች ውበትና ለምግብ ዋስትና መረጋገጥ ተጨማሪ አቅም እየሆነ ነው
Jul 3, 2026 231
ጅማ፤ ሰኔ 26/2018 (ኢዜአ)፡- አረንጓዴ አሻራ ለከተሞች ውበት ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የሥራ ዕድልን ለማስፋት ተጨማሪ አቅም መሆኑን የጅማ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በኢትዮጵያ በይፋ ከተጀመረበት ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን በአየር ንብረት፣ በምግብ ዋስትና፣ በማህበራዊ እና በኢኮኖሚ ዘርፎች በርካታ ተጨባጭ ውጤቶች ተመዝግበዋል። በጉዳዩ ዙሪያ ኢዜአ ያነጋገራቸው የጅማ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን እንዳሉት፤ የአረንጓዴ አሻራ የማህበረሰቡን የደን ልማትና እንክብካቤ ግንዛቤ ከማሳደጉም በላይ የአየር ንብረት መዛባትን ለመከላከል ከፍተኛ ድርሻ እያበረከተ ይገኛል። በጅማ ዩኒቨርሲቲ ግብርና እና እንስሳት ሕክምና ኮሌጅ የተፈጥሮ ሀብት አጠባበቅ ትምህርት ክፍል መምህር እና ተመራማሪ ጌትነት ሰይድ፤ መርሃ ግብሩ የአየር ንብረት ለውጥንና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ ማስቻሉን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩ ከበጋው ወቅት አፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ጋር መተሳሰሩም የከርሰ ምድርና የገጸ ምድር ውሃ ሀብት እንዲጎለብት በማድረግ ለመስኖ ልማት ተጨማሪ አቅም መሆኑን አስረድተዋል። ለምግብነት የሚውሉ እና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው ችግኞች መተከላቸውም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከቱ መሆኑን ጠቁመው፤ የሚተከሉ ችግኞች ከየአካባቢው ሥነ-ምህዳር እና የአየር ንብረት ሁኔታ ጋር እንዲስማሙ ለማድረግ የባለሙያዎችና የተመራማሪዎች ሚና ወሳኝ መሆኑን አክለዋል። በዩኒቨርሲቲው የተፈጥሮ ሀብት አጠባበቅ ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ጥበቡ አለሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄ የማህበረሰቡን የአካባቢ ጥበቃ ባህል ከፍ ማድረጉን ተናግረዋል። ይህም የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙና የደረቁ ምንጮችን በመመለስ ለብዝሃ ሕይወት መጠበቅ ተጨማሪ አቅም መሆናቸውን ጠቁመዋል። የሚተከሉት ችግኞች ሀገር በቀል መሆናቸው የአካባቢውን ሥነ-ምህዳር ተቋቁመው ለመጽደቅ እንዳስቻላቸው የገለጹት ዶክተር ጥበቡ፤ ችግኞችን ከመትከል ባለፈ በመንከባከብ ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታውን ለማጉላት የሁሉም አካላት ርብርብና ድርሻ ያስፈልጋል ብለዋል።
በመዲናዋ የአካባቢ ጥበቃን ከኢንዱስትሪ ልማት ጋር ያቀናጀ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እየተጠናከረ መጥቷል
Jul 3, 2026 289
አዲስ አበባ ፤ሰኔ 26/2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ ከተማ የአካባቢ ጥበቃን ከኢንዱስትሪ ልማት ጋር ያቀናጀ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን የከተማዋ ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ጃንጥራር አባይ አስታወቁ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሰራተኞችና የአምራች ኢንዱስትሪ ባለቤቶች ዛሬ ማለዳ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 ቦሌ ቡልቡላ ፓርክ ተገኝተው አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። ምክትል ከንቲባው አቶ ጃንጥራር አባይ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የተተገበሩና እየተተገበሩ የሚገኙ የአረንጓዴ ልማት ፕሮጀክቶች የመዲናዋን ገጽታ፣ የነዋሪዎችን ህይወትና የኢኮኖሚ ግንባታን እያረጋገጡ ነው። ቀደም ሲል ክፍት እና የቆሻሻ መጣያ የነበሩ ስፍራዎች አሁን ላይ ወደ አረንጓዴነት ተቀይረው ውብ እና አዲስ እየሆኑ መምጣታቸውንም አብራርተዋል። እነዚህ ስፍራዎች ለከተማዋ ነዋሪዎች መዝናኛ ከመሆን ባለፈ፣ ለውጭ ሀገር ጎብኝዎች የቱሪስት መዳረሻነት እያገለገሉ እንደሚገኙም ጠቁመዋል። በተጨማሪም በመዲናዋ በርካታ ችግኞች መተከላቸው የከተማዋን የአየር ንብረት ሚዛን ለመጠበቅ ከፍተኛ እገዛ እያደረገ መሆኑን አመልክተዋል። ከዚህ በፊት ቢሮው በመዲናዋ በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች የራሱን የላቀ ሚና ሲያበረክት መቆየቱን የገለጹት ምክትል ከንቲባው፤ በከተማዋ የሚተከሉ ችግኞች ጸድቀው ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ በማድረግ ረገድም ስኬታማ ተግባር ማከናወኑን ተናግረዋል። በዘንድሮው ዓመትም ከማዕከል እስከ ወረዳ ያሉ አመራር አባላትን፣ ሰራተኞችንና የኢንዱስትሪ ባለቤቶችን በማስተባበር ልዩ ልዩ ፋይዳ ያላቸውን ችግኞች ለመትከል ወደ እንቅስቃሴ መገባቱን ገልጸዋል። ደኖች ከአምራች ኢንዱስትሪዎች የሚለቀቁ ሙቀት አማቂ ጋዞችን ለማስወገድ አይተኬ ሚና እንዳላቸው የጠቆሙት ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ሃላፊው አቶ ጃንጥራር፤ በመዲናዋ የኢንዱስትሪ ልማትን ከአካባቢ ጥበቃ ጋር በማስተሳሰር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ለማጠናከር ትኩረት መደረጉን አመልክተዋል።