አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በብሔረሰብ አሥተዳደሩ በሞዴል መንደሮች የገጠር ኮሪደር ልማት ሥራ ይከናወናል
Jan 16, 2026 100
ሰቆጣ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡- የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አሥተዳደር በሰባት ሞዴል መንደሮች የገጠር ኮሪደር ልማት ሥራ ለማከናወን ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታወቀ። በአሥተዳደሩ የገጠር ኮሪደር ልማትን ለማሳካት ያለመ የንቅናቄ መድረክ ዛሬ በሰቆጣ ከተማ ተካሂዷል። የብሔረሰብ አሥተዳደሩ የገጠር ክላስተር አስተባባሪና የመንገድ መምሪያ ኃላፊ ፀጋው እሸቴ በዚሁ ወቅት፤ ከዚህ ወር መጨረሻ ጀምሮ ወደ ተግባር የሚገባው የገጠር ኮሪደር ልማት በሕዝብ ተሳትፎ ታጅቦ ይከናወናል ብለዋል። በሁሉም ወረዳዎች ሰባት ሞዴል መንደሮችን በመለየት የገጠር ኮሪደር ልማት እንደሚከናወን የገለጹት ደግሞ የብሔረሰብ አሥተዳደሩ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አዲስ ወልዴ ናቸው። በገጠር ኮሪደር ልማት ቅንጅታዊ አሠራርን በመከተል የአርሶ አደሩን ኑሮ ለማሻሻል እንደሚሠራ ጠቁመዋል።
በአስተዳደሩ የተከናወነው የተፋሰስ ልማት ስራ አርሶ አደሮች ከተረጂነት እንዲወጡ አስችሏል
Jan 16, 2026 91
ድሬዳዋ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡-በድሬዳዋ አስተዳደር ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች ከተረጂነት ለመውጣት እንዳስቻላቸው አርሶአደሮች ተናገሩ። በተፋሰሱ እና በሌሎች የገጠር ልማቶች በተከናወነው ስራ በመታገዝ ዘንድሮ ከ38 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ከተረጂነት ወደ አምራችነት እንደሚሸጋገሩ አስተዳደሩ አስታውቋል ። ባለፉት ዓመታት የተሰሩት ልማቶች የተፈጥሮ ሃብት ይዞታን በመመለስ፣ የጎርፍ ችግርን በመከላከልና ምንጮችን በመመለስ ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ማስቻሉን ዘንድሮ በተጀመረው የተፋሰስ ልማት እየተሳተፉ የሚገኙ አርሶአደሮች ለኢዜአ ገልጸዋል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል የገንደ ሪጌ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ሱልጣን ፈጃል እንደገለፁት፤ ተፋሰሱ ተጨማሪ የእርሻ መሬትና ውሃን እንዲጠቀሙ በማስቻሉ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተው ህይወታቸውን ለመለወጥ አስችሏቸዋል። ቀደም ብለው ዓልምተው የነበረው ብርቱካን ባለፈው ሳምንት ተሰብስቦ ከ900 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን እንደአብነት አንስተዋል። ከብርቱካን በተጨማሪ ሽንኩርት፣ ሃባብና ሎሚ እያመረቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። .የኡሉል ሞጆ ቀበሌ አርሶአደር ወይዘሮ ሐሊማ መሐመድ በበኩላቸው፣የተፋሰስ ልማቱ ለግብርና ስራ ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩ አርሶአደሩ በምንጭና በዝናብ ውሃ በዓመት ከሁለት ጊዜ በላይ እያመረተ መሆኑን ተናግረዋል። ይሄን የመሰለ የተፈጥሮ ፀጋና ጉልበት እያለን ለልመና እጅ አንዘረጋም ያሉት አርሶአደር ሐሊማ፤ ከራሳችን አልፈን ለተቸገሩ ለመርዳት ጠንክረን እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። በተፋሰስ ልማትና በሌማት ትሩፋት በተፈጠሩላቸው እድሎችና ድጋፎች በመታገዝ ከተረጂነት ወደ አምራችነት በመሸጋገር ከልማታዊ ሴፍትኔት መውጣታቸውን የገለፁት ደግሞ ሌላው የኡሉል ሞጆ ቀበሌ አርሶአደር ኡስማን መሐመድ ናቸው። የቀበሌው ህብረተሰብ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የመሸጋገርን መርህ ለማሳካት በተፋሰስ ልማትንም ሆነ በሌሎች ስራዎች እየተጋ መሆኑን አንስተዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኑረዲን አብደላ፤ ባለፉት ዓመታት በድሬዳዋ የገጠር ቀበሌዎች በሚገኙ 57 ሺህ ሄክታር የተራቆቱ ተፋሰሶች ላይ የተለያዩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። በተከናወኑት ተግባራት ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በአነስተኛ መስኖ ልማት በመሰማራት አበረታች ውጤት መገኘቱን የገንደ ሪጌ ገጠርን በአብነት ጠቅሰው አስረድተዋል። እንደ ኃላፊው አቶ ኑረዲን ገለፃ እየተከናወኑ የሚገኙ አበረታች የገጠር ልማቶች ከተረጂነት ወደ አምራችነት የመሸጋገሩን ጉዞ ስኬታማ ያደርጉታል። በዘንድሮ በጀት አመት 38 ሺህ በልማታዊ ሴፍትኔት የታቀፉ አርሶአደሮችና አርብቶአደሮች ወደ አምራችነት ይሸጋገራሉ ብለዋል።
በዞኑ የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በ631 ተፋሰሶች ላይ እየተካሄደ ነው
Jan 16, 2026 87
ወልዲያ ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡-በሰሜን ወሎ ዞን የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በ631 ተፋሰሶች ላይ እየተካሄደ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የተፈጥሮ ሃብት ባለሙያ አቶ ጋሻው አለሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ባለፉት አመታት የተከናወነው የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ደርቀው የነበሩ ምንጮች እንደገና በመፍለቃቸውና የከርሰ ምድርና ገጸ-ምድር የውሃ አቅም በመጨመሩ አርሶ አደሩ በስራው በንቃት እንዲሳተፍ አድርጓል። የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአፈር ለምነትን በማሳደጉና የውሀ አማራጮች መስፋታቸው ለመስኖ ልማት ስራው ስኬት ተጨማሪ አቅም መፍጠራቸውን ገልጸዋል። ስራዎቹ ተራቁተው የነበሩ ተራሮችን ወደ ልምላሜ በመመለሳቸው አርሶ አደሩ በመኖ ልማትና በንብ ማነብ ስራ በመሰማራት ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እንዳስቻለው ተናግረዋል። በዘንድሮው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ 380 ሺህ 493 አርሶ አደሮች 631 ተፋሰሶችን እያለሙ መሆኑን አስረድተዋል። በዘንድሮው የአፈርና ውሃ እቀባ ልማት ስራም 443 ሺህ 77 ሄክታር መሬት ላይ የማሳና የተራራ ላይ እርከንና ሌሎች ስነ አካላዊ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዞኑ የመቄት ወረዳ የ029 ቀበሌ ነዋሪ አቶ አባቡ ዋለልኝ፣ ባለፉት ዓመታት ከተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ያገኘናቸውን ጥቅሞች ዘንድሮም ለማስቀጠል በትጋት እየሠራን ነው ብለዋል። ባለፉት ዓመታት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች አካባቢዎች አገግመው ለእንስሳት መኖ፣ ንብ ማነብና ሌሎች ስራዎች ጥቅም በመስጠታቸው ዘንድሮ በራሳቸው ተነሳሽነት ለስራ መውጣታቸውን ተናግረዋል። ባለፉት አምስትና ስድስት ዓመታት ባከናወኗቸው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች ዘርፈ-ብዙ ጥቅሞችን አግኝተንበታል ያሉን ደግሞ በላስታ ወረዳ የጠልፈጢት ቀበሌ ነዋሪ አቶ ታደሰ ዳምጤ ናቸው። በዚህም በጓሮአቸው በአነስተኛ መስኖ አትክልት በማልማት፣ መኖ በማጨድ በእንስሳት እርባታና ማድለብ ስራ በመሰማራት ተጨማሪ ሃብት ለማፍራት እንዳስቻላቸው አስረድተዋል። በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተሰራው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራ የዞኑን የደን ሽፋን ከ20 በመቶ በላይ ማድረሱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በአካባቢ ጥበቃ ልማት የተሠሩ ሥራዎች ጤናማ ትውልድ ለማፍራት ከፍተኛ ፋይዳ አላቸው
Jan 16, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃና አረንጓዴ ልማት የተሠሩ ሥራዎች ጤናማ ትውልድ ለማፍራት የጎላ ፋይዳ እንዳላቸው በዓለም አቀፍ የጤና ተቋማት የሚሠሩ የጤና ባለሙያዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ የሕጻናት ሄማቶሎጂና ኦንኮሎጂ ማኅበር የምሥረታ መርሐ-ግብር በአዲስ አበባ ተካሂዷል። በመርሐ-ግብሩ የተሳተፉ የጤና ባለሙያዎች ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የተከናወኑ የአካባቢ ጥበቃና የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች ጤናን ለመጠበቅ፣ ለስፖርታዊ እንቅስቃሴ እና ለማኅበራዊ ግንኙነቶች ያላቸው ፋይዳ ከፍተኛ ነው። በአውስትራሊያ የጤና ባለሙያ የሆኑት ብሮንዊን ማክናማራ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ ከተማ በአካባቢ ንጽህና፣ አረንጓዴ ቦታዎችና ፓርኮችን በማስፋፋት ረገድ ከዚህ ቀደም ከሚያውቁት የተለየ ለውጥ ማየታቸውን ተናግረዋል። የፕላስቲክና የኬሚካል ውጤቶች የጤና ጉዳት የሚያስከትሉ በመሆኑ ብክለትን ለመከላከል እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችንም አድንቀዋል። የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ለጤና አጠባበቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ያስረዱት ደግሞ የቶሮንቶ ዩንቨርሲቲ ፕሮፌሰር ሺላ ዋይትዝማን ናቸው። አረንጓዴና ንጹህ አካባቢ ጤናን ለመጠበቅ ከሚያስችሉ ጉዳዮች አንዱ መሆኑን ገልጸው፤ በሽታን አስቀድሞ መከላከል ከማከም የተሻለ ነው ብለዋል። በ’ፒውር ኧርዝ’ የምሥራቅ አፍሪካ ዳይሬክተር ፍሬው ከፍያለው በአካባቢ ጥበቃ ተሟጋችነትና ወጣቶችን በማሳተፍ የጽዳት ሥራዎች ላይ ለበርካታ ዓመታት እየሠሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል።
በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ምርትና ምርታማነትን አሳድጓል
Jan 15, 2026 191
ሮቤ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦በባሌ ዞን ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የዞኑ አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የ2018 የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በጎሮ ወረዳ ወልተኢ ጨፋ ቀበሌ ደራርቱ ተፋሰስ ላይ ዛሬ ተጀምሯል። ከወረዳው አርሶ አደሮች መካከል አህመድ መሐመድ እንዳሉት፤ ባለፉት ዓመታት በአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ የተራቆቱ መሬቶች መልማታቸው የንብ ማነብ ሥራን ለማከናወንና ምርታማነትን ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ ፈጥሮላቸዋል። በዘንድሮ የበጋ ወቅትም ከአምናው የተሻለ የልማት ሥራ ለማከናወን ከአካባቢያቸው አርሶ አደሮች ጋር በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን አመልክተዋል። በተፋሰስ ልማት ስራ የአካባቢ መራቆትን ከመከላከል ባለፈ ደርቀው የነበሩ ምንጮች መልሰው መመንጨት ጀምረዋል ያሉት ደግሞ አርሶ አደር ሀሰን አብዶ ናቸው። ከዚህ ቀደም በለሙ ተፋሰሶች ውስጥ የተተከሉ እጽዋቶች በመጽደቃቸውና እርጥበታማ አየር እንዲኖር በማስቻሉ የግብርና ስራን በተሻለ መልኩ በማከናወን ድርቅን ለመቋቋም እያገዛቸው መሆኑን ነው የተናገሩት። አርሶ አደር ሐምዛ ቃዲ በበኩላቸው እንዳሉት ባለፉት ዓመታት በተፋሰስ ልማት ሥራ በተሰሩ ሥራዎች ከምርት ውጭ ሆኖ የነበረ የእርሻ መሬታቸው በማገገሙ እስከ 40 ኩንታል የስንዴ ምርት ማግኘት ችለዋል። አርሶ አደሮቹ እንዳሉት የተፋጥሮ ኃብት ጥበቃና የእንክብካቤ ሥራን በማጠናከር ምርታማነታቸውን ይበልጥ ለማሳደግ የጀመሩትን ሥራ አጠናክረው ይቀጥላሉ። የጎሮ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ እሸቱ ተክሌ በበኩላቸው፣ በወረዳው ባለፉት ዓመታት በቅንጅት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የአካባቢውን አየር ንብረት ከማስተካከል ባሻገር ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል ምንጭ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት በተከናወነ የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈር ለምነት በመጨመሩ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን የገለጹት ደግሞ የባሌ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሙአዊያ ፉአድ ናቸው፡፡ በዘንድሮው የበጋ ወራትም ሥራውን በተቀናጀ መንገድ አጠናክሮ በማስቀጠል የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ከ549 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ያሳተፈ ሥራ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡ ዘንድሮ በሚካሄደው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማትም በ166 ተፋሰሶች ላይ ከ84 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ስነ አካላዊ ስራዎች ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል። በመርሐግብሩ ላይ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ተወካይ አቶ ሴይፋዲን ሀሰን፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ምርታማነትን ለማሳደግ ከሚያበረክተው ጠቀሜታ በተጨማሪ ለቀጣዩ ትውልድ የለማና አረንጓዴ ሀገርን የማስረከብ ዓላማ ያለው በመሆኑ ስራው ተጠናክሮ እንዲቀጥል ድጋፍና ክትትል ይደረጋል ብለዋል።
በክልሉ የተፋሰስ ልማት ውጤትን በማስቀጠል የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል - ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር)
Jan 15, 2026 99
ሾኔ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተፋሰስ ልማት ውጤትን አጠናክሮ በማስቀጠል የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የክልሉ የ2018 የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በሀዲያ ዞን ምስራቅ ባዳዋቾ ወረዳ አምቡርሴ አንጁሎ ቀበሌ በአንጁሎ ንዑስ ተፋሰስ ላይ ተጀምሯል። ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) መርሃ ግብሩን ባስጀመሩበት ወቅት እንደተናገሩት በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወነ የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈርን ለምነት በመጨመሩ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ተችሏል፡፡ ዘንድሮው በበጋ ወራትም ሥራውን በተቀናጀ መንገድ በማስቀጠል የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ አርሶ አደሮችን ያሳተፈ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊና የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ኡስማን ሱሩር በበኩላቸው ያለፉት ዓመታት የተፋሰስ ልማት ሥራዎች በክልል ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እያገዙ ነው። በዚህም በ2015 የምርት ዘመን 142 ሚሊየን ኩንታል የነበረው ክልላዊ የምርት መጠን በ2017 ወደ 159 ሚሊየን ኩንታል በማደጉ ገበያም ማረጋጋት የሚያስችል አቅም ተፈጥሯል ብለዋል። በተራቆቱ አካባቢዎች የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የእንስሳት መኖ ልማትን በማሳደግ የወተት ምርታማነትን በተመሳሳይ ዓመት ከነበረበት 321 ሚሊየን ሊትር ወደ 675 ሚሊየን ሊትር ማሳደጉን ተናግረዋል፡፡ ተግባሩን በማስቀጠል በዘንድሮ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማትም በ1ሺህ 294 ንዑስ ተፋሰሶች ላይ ከ290 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል።
በዞኑ ከ273 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚሸፍን የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ መካሄድ ጀምሯል
Jan 14, 2026 187
አምቦ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን ከ273 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚሸፍን የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ መካሄድ መጀመሩን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በዞን ደረጃ የሚካሄደው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በአምቦ ወረዳ ኢላሙ ጎሮምቲ ቀበሌ በይፋ ተጀምሯል። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የልማትና የዕድገት ግቦችን ለማሳካት እያገዘ ነው የምዕራብ ሸዋ ዞን ምክትል አስተዳደሪ አቶ አበበ ጨመዳ በወቅቱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት አመታት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአፈር ለምነት እንዲመለስ አድርጓል። በዚህ የበጋ ወራትም ተግባሩን በማስቀጠል ለሁለት ወራት የሚቆይ የተቀናጀ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ዘመቻ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ ከ273 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ እንደሚከናወን ተናግረዋል፡፡ በዘመቻ መልክ በሚካሄደው በዚህ ስራ ከ600 ሺህ በላይ የዞኑ ነዋሪዎች ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም አስረድተዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብዲሳ ሀይሉ በበኩላቸው፤ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራውን ውጤታማ ለማድረግ በየደረጃው ላሉ የግብርና ባለሙያዎች፣ ለአርሶ አደሮች እና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ስልጠና መሰጠቱን ተናግረዋል፡፡ የአምቦ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሰረት ጉዲሳ እንዳሉት፤ ባለፉት ጊዜያት በወረዳው በተከናወኑት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ከልማት ወጪ የነበሩ አካባቢዎች ዳግም ወደ ልማት ገብተዋል። ህብረተሰቡም ጥቅሙን በመረዳቱ በተፋሰስ ልማቱ በነቂስ ወጥቶ እየተሳተፈ መሆኑን ጠቅሰው በወረዳው ከ2 ሺህ 700 ኪሎ ሜትር መሬት በላይ የእርከን፣ የስነ-ህይወታዊና የስነ-አካላዊ ስራዎች ይከናወናል ብለዋል። የአምቦ ወረዳ ኢላሙ ጎሮምቲ ቀበሌ አርሶ አደሮች የተፋሰስ ልማት ስራው ተግባራዊ ከመሆኑ በፊት የእርሻ ማሳቸው ለም አፈር በጎርፍ በመጠረጉ ምርታማነታቸው መቀነሱን ጠቁመዋል። ችግሩን ለማቅረፍም በየአመቱ በሚከናወነው የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መሳተፋቸውን አስረድተዋል። በተፋሰስ ልማቱ ባለፉት ዓመታት የተሰሩ አፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአፈር መሸርሸርን አስቀርቷል ብለዋል።ይህም የሰብል ምርታቸው እንዲጨምር ማድረጉን ተናግረዋል።
በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የተፋሰስ ልማት ስራ ተጨባጭ ውጤት አምጥቷል
Jan 13, 2026 164
ግራዋ ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የተፋሰስ ልማት ስራ ተጨባጭ ውጤት ማምጣቱ ተገለጸ። በዞኑ የዘንድሮ በጋ ተፋሰስ ልማት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የዞን ደረጃ በግራዋ ወረዳ በሜይራ ጉዲና መንደር ተጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የምስራቅ ሐረርጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ሚስኪ መሀመድ፤ በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የተፋሰስ ልማት ስራ አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ ለምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ አድርጓል ብለዋል። በተለይም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ አንጻር የተፋሰስ ልማት ስራ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አብራርተዋል። የኦሮሚያ ክልል መሬት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ መሰርት አሰፋ በበኩላቸው፤ የሐረርጌ አርሶ አደሮች በተፋሰስ ልማት ባገኙት ውጤት አካባቢያቸውን መቀየር መቻላቸውን አንስተዋል። በዞኑ ተጎሳቅሎ የነበሩ አካባቢዎችን መልክአ ምድር በመጠበቅና የአፈር ለምነትን በማሻሻል አረንጓዴ መላበሱን ገልጸው ይህም የተፋሰስ ልማት ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። የግራዋ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አብዲሻ ጃፈር የዘንድሮው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ከሰባት ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የሚከናወን መሆኑን ገልፀዋል። በተፋሰስ ልማቱ ላይ የተሳተፉ አርሶ አደሮች ባለፉት አመታት በሰሩት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ በርካታ ጥቅም እንዳስገኘላቸው ተናግረዋል።
የተፈጥሮ ሃብቶቻችንን በሁሉም መልክ ማልማት የሰርክ ተግባራችን ሊሆን ይገባል-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jan 13, 2026 154
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ የተፈጥሮ ሃብቶቻችንን በሁሉም መልክ ማልማት የሰርክ ተግባራችን ሊሆን ይገባል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመለከቱ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት የአካባቢ ጥበቃ ስርአታችን ደካማ በመሆኑ በድጋሚ ለመተካት እጅግ አስቸጋሪና ለም የሆነውን አፈራችንን ስናጣ ቆይተናል ሲሉ ገልጸዋል። በህዝብና በመንግስት ትብብር የተጀመረው የአካባቢ ጥበቃ ሥራ የዝናብ ወራት ከመቃረቡ በፊት በዚህ መልክ መሰራት መጀመሩ ተስፋ ሰጪ መሆኑን አመልክተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው፤ የተፈጥሮ ሃብቶቻችንን በሁሉም መልክ ማልማት የሰርክ ተግባራችን ይሁን፤ እንበርታ፣ እጆቻችን አፈር ይንኩ፣ሀገር እናልማ ሲሉ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው የአካባቢውን ስነምህዳር በመጠበቅ ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል
Jan 13, 2026 255
አሶሳ፤ ጥር 5/2018 (ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሲከናወን የቆየው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአካባቢውን ስነምህዳር በመጠበቅ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የዘንድሮው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ደረጃ አሶሳ ዞን ቡልድግሉ ወረዳ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እና የአካባቢው ነዋሪዎች በተገኙበት ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ባበክር ሀሊፋ በወቅቱ እንደገለጹት፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአካባቢውን ስነምህዳር በመጠበቅ ምርታማነት እንዲጨምር አድርጓል። በተለይም የተፋሰስ ልማት ስራ በሚከናወንባቸው አካባቢዎች የሚተከሉ ችግኞች አፈርና ውሃን ከመጠበቅ ባለፈ ለአርሶአደሩ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እያስገኙ ነው ብለዋል። በዘንድሮው ዓመት ከ57 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ለማከናወን እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ህብረተሰቡ ጥቅሙን በመረዳት በየአካባቢው ተሳትፎውን እያሳደገ መሆኑን ጠቅሰዋል። በክልሉ እየተከናወነ የሚገኘው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በደለል እንዳይሞላ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውም ኃላፊው አንስተዋል። የቡልድግሉ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ በክሪ አብዱላሂ በበኩላቸው፤ በወረዳው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መከናወን ከጀመረ ወዲህ የደን ሽፋን እያደገ እና የአካባቢው አየር ንብረት እየተስተካከለ መምጣቱን ተናግረዋል። ወረዳው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ አቅራቢያ በመገኘቱ የሚከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው የጎላ ጠቀሜታ እንዳለው አክለዋል። በመርሃግብሩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የልማትና የዕድገት ግቦችን ለማሳካት እያገዘ ነው
Jan 13, 2026 214
በደሌ፤ ጥር 5/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል እየተከናወነ የሚገኘው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የልማትና የዕድገት ግቦችን ለማሳካት እያገዘ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በኦሮሚያ ክልል ለቀጣዮቹ ሁለት ወራት የሚከናወነው የዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ስራ በዛሬው ዕለት በክልል ደረጃ በቡኖ በደሌ ዞን ዳቦ ሐና ወረዳ ተጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ፣ የዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ስራ ከ6 ሺህ 300 በላይ ተፋሰሶች ላይ ይከናወናል ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በክልሉ በተከናወነው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የክልሉ የደን ሽፋን መጨመሩንና በብዙ ተጎድተው የነበሩ አከባቢዎች በማገገማቸው ምርታማነትም በመጨመር ላይ እንደሚገኝ አንስተዋል። የተፋሰስ ልማት ስራው በተለይም በግብርናው ዘርፍ ተቀርጸው እየተተገበሩ የሚገኙ ኢንሼቲቮች ስኬት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በአጠቃላይ በክልሉ እየተከናወነ የሚገኘው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የልማትና የዕድገት ግቦችን ለማሳካት ትልቅ አበርክቶ አለው ብለዋል። ዘንድሮም በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ በጠንካራ የህዝብ ተሳትፎ ታጅቦ የሚከናወን መሆኑን ገልጸዋል። የቡኖ በደሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አማን ደኑ በበኩላቸው በዞኑ የተጀመረው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በ222 ተፋሰሶች ላይ የሚከናወን መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ በአየር ንብረት ለውጥ እና በአፈር አሲዳማነት ምክንያት የሚደርሰውን የምርታማነት መቀነስን ለመከላከል በተፋሰስ ልማቱ የሚከናወኑ ስራዎች እንደሚጠናከሩ ተናግረዋል። በበጋው ወራት የተፋሰስ ልማት የሚከናወንበት መሬት በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተለያዩ ቸግኞች ለመሸፈን የቅድመ ዝግጅት ስራ እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል። ለዚህም ከ200 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በዞኑ እየተዘጋጁ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተፋሰስ ልማት ስራው የተሳተፉ አርሶ አደሮችም ስራው በአፈርና እና ውሃ ሀብቶች ላይ የሚደርሱ ችግሮችን በመከላከል ተጠቃሚነታቸውን የሚያረጋግጥ በመሆኑ ዘንድሮም ተሳትፏቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል።
በመዲናዋ እየተከናወነ ያለው የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራ አካታች እና ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን የያዘ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jan 12, 2026 172
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ እየተከናወነ ያለው የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራ አካታች እና ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን የያዘ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። በአዲስ አበባ በሚገኙ ስምንት ወንዞች ላይ 47 ኪሎ ሜትር የሚረዝም የወንዝ ዳርች ልማት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። ከንቲባዋ ይህን ያሉት በከተማዋ እየተገነቡ ከሚገኙ ስምንት የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች መካከል የቀበና እና የግንፍሌ ወንዞችን የሥራ ሂደት በገመገሙበት ወቅት ነው። ከንቲባ አዳነች አቤቤ ወንዞች ለከተማ መቆርቆር፣ ለከተማ ውበት እና ለከተማ ልማት ዋና እና መሰረት ናቸው ሲሉም ገልጸዋል። ይሁንና በአዲስ አበባ ወንዞች የብክለት ችግር የሚፈጠርባቸው፣ የተለያዩ ወንጀለኞች የሚደበቁበት፣ የበሽታ መንስኤዎች በመሆን ብዙ ተጽእኖዎችና ችግሮች ሲያደርሱ መቆየታቸውን አመልክተዋል። በኢትዮጵያ ወንዞች ላይ በተደረገ ጥናት በመዲናዋ ብቻ 76 ወንዞች እንዳሉ ጠቁመው ወንዞቹ ከየመጸዳጃ ቤቱ ፍሳሽ የሚገባባቸው ሆነው መገኘታቸውን ነው የገለጹት። በለውጡ ዘመን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ወንዞቻችንን እናጽዳ ሸገርን እናስውብ በሚል አዲስ አበባን እንደ ስሟ አበባ ከማድረግ ራዕይ ጋር በማስተሳሰር በ2012 ዓ.ም የወንዞች ዳርቻ ልማት መጀመሩን አስታውሰዋል። ስራው አዲስ አበባ ውብ አበባ መሆን የምትችለው ወንዞች ከጸዱ እና ወደ ተፈጥሯዊ ማንነታቸው ከተመለሱ እና ከዳኑ ብቻ እንደሆነ በትልቅ መረዳት የተጀመረ እንደሆነም ነው ያስረዱት። የወንዝ ዳርቻ ልማት በወቅቱ ለኢትዮጵያ አዲስ በመሆኑ የውጭ የፋይናንስና የቴክኒክ ድጋፍ አስፈልጎ እንደነበር አመልክተዋል። ፕሮጀክቱ በተጀመረ አምስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ሁለት ኪሎ ሜትር የሚሆን ብቻ ልማት መከናወኑን ጠቅሰው በራሳችን ሀገር በቀል አቅም ለምን አንሰራም? በሚል የዛሬ ዓመት በአዲስ መልክ ስራው መጀመሩን ጠቁመዋል። በኢትዮጵያውያን አቅም በስምንት ወንዞች ላይ የ47 ኪሎ ሜትር የውንዝ ዳርቻ ልማት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም አብራርተዋል። ከዚህ ውስጥ ትልቁን ድርሻ የሚይዘው ከእንጠጦ እስከ ፒኮክ ያለው መሆኑን ገልጸው የውስጥ ለውስጥ መንገዶች እና መሰረተ ልማቶችን ሳይጨምር 21 ኪሎ ሜትር እንደሚረዝም ገልጸዋል። ከእንጠጦ እስከ ፒኮክ ባለው የወንዝ ዳርቻ ውስጥ ሰባት ፓርኮች እንደሚገኙና ንግድን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶችን እንደሚሰጡም ተናግረዋል። በአጠቃላይ የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራው አካታች እና ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን የያዘ መሆኑን አክለዋል።
የውሃ ሃብት ሁሉንም የህይወት ዘርፍ የሚነካ ወሳኝ አህጉራዊ የህልውና ጉዳይ ነው
Jan 12, 2026 164
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ የውሃ ሃብት ለአፍሪካውያን ሁሉንም የህይወት ዘርፍ የሚነካ ወሳኝ አህጉራዊ የህልውና ጉዳይ መሆኑን የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። 39ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤና 48ኛው የሥራ አስፈፃሚዎች ምክር ቤት ስብሰባ ከየካቲት 4 እስከ 8 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ የአፍሪካ ሕብረት መሰብሰቢያ አዳራሽ ይካሄዳል። የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤን አጀንዳ፣ የውሳኔ ሀሳብና ሪፖርት ለማዘጋጀት የሚደረገው 51ኛው የሕብረቱ አባል ሀገራት ቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ ስብሰባ ዛሬ ተጀምሯል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ትኩረቱን በውሀ ላይ ያደረገ ነው። የውሃ ሃብት ለአፍሪካውያን ሁሉንም የህይወት ዘርፍ የሚነካ ወሳኝ አህጉራዊ የህልውና ጉዳይ ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፤ የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤና ኮፕ 30ን ለመከታተል ትክክለኛ ምርጫ ነው ብለዋል። የኮፕ 32 በአፍሪካ ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ በመመረጧ ኩራት ይሰማናል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረትና የተባበሩት መንግሥታት ለጉባኤው ዝግጅት በጋራ እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። 39ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ በሰላምና ጸጥታ ዙሪያ ብዙም ለውጥ ባልታየበት ሁኔታ እንደሚካሄድ ገልጸው፤ በሱዳን፣ ሊቢያ፣ በሳህል ቀጣና እና በምስራቃዊ ዲሞክራቲክ ኮንጎ ያለው ችግር እስካሁን አልተፈታም ብለዋል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን የሰላምና ደህንነት ምክር ቤት የአፍሪካ ችግሮች በአፍሪካውያን መፍትሔ እንዲያገኙ ለማስቻል በሰላምና ደህንነት የሪፎርም በጋራ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት ላይ የሚጣሉ የታሪፍ ገደቦች፣ የሚሰበሰበው ሀብት መቀነስና የጉዞ ክልከላዎች የዓለም ህግና ሥርዓቱን በመሸርሸር አሉታዊ ተፅዕኖ እያሳደሩ መሆኑንም አንስተዋል። በመሆኑም ይህንን ኢ-ፍትሐዊነት ለመከላከል በሕብረቱ አባል ሀገራት መካከል ትብብርና አንድነትን ማጠናከር ይገባል ብለዋል። በአፍሪካ ሕብረት የአንጎላ ቋሚ ተወካይ እና 51ኛው የሕብረቱ አባል ሀገራት ቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ ስብሰባ ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ሚጉኤል ቤምቤ በአፍሪካ ዘላቂ የውሃ ሀብት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ መሪ ሀሳብ ውኃን መሰረት ያደረገ መሆኑን በማንሳት፤ በአፍሪካ በውኃ ጉዳዮች ላይ የሚነሱ ግጭቶችን መፍታት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ይመክራል ብለዋል፡፡ የዚህን መሪ ሀሳብ አመንጪ ኢትዮጵያ መሆኗን ያስታወሱት ፕሮፌሰር ሚጉኤል፤ ለአፍሪካውያን የቀረበ ሀሳብ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ በአፍሪካ ቀጣናዊ ትብብርና ኢኮኖሚያዊ ውህደት ለመፍጠር የኢንዱስትሪ አብዮት ወሳኝ መሆኑን በመግለጽ፤ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና በሁሉም አባል ሀገራት ገቢራዊ መደረግ አለበት ነው ያሉት፡፡ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና የአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 አካል ነው ያሉት ፕሮፌሰር ሚጉኤል፤ አህጉራዊ ግቦችን ለማሳካት ትብብርን ማጠናከር እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡
በሲዳማ ክልል የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራው የአርሶ አደሩን ምርታማነት በመጨመር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያሳደገ ነው
Jan 12, 2026 101
ሀዋሳ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራው የግብርና ምርታማነትን በመጨመር የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደገ መሆኑ ተገለጸ፡፡ በክልሉ የ2018 በጀት ዓመት የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ ንቅናቄ መድረክ ዛሬ በሃዋሳ ከተማ ተከናውኗል፡፡ የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አብርሃም ማርሻሎ በዚህ ወቅት እንደገለጹት በክልሉ የተከናወነው የአፈርና ውሃ ልማትና ጥበቃ ሥራ የግብርና ምርታማነትን በመጨመር የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ነው፡፡ በአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራው ህዝብን በባለቤትነት በማሳተፍ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን ተናግረዋል፡፡ ለዚህም በተራራማ አካባቢዎች ጠረጴዛማ እርከን መስራትና የተጎዱ መሬቶች በስነ ህይወታዊ እና በስነ አካላዊ ዘዴ እንዲያገግሙ መደረጉን ገልጸዋል። በዚህም በየአካባቢው የከርሰ እና ገጸ ምድር ውሀ ሀብት በመጨመሩ የአርሶ አደሩ ምርታማነትና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያደገ መጥቷል ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማቶች የተገኙ ስኬቶችን በማስቀጠል ዘንድሮም ህብረተሰቡን ያሳተፈ ሥራ እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአፈር መሸርሸርን የመከላከል፣ የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ የማድረግና የውሃ አውታሮችን የማስፋት ስራ ተከናውነዋል ብለዋል። በ2017 በጀት ዓመት በ668 ንኡስ ተፋሰሶች ላይ በተከናወነ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ከ136 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት መልማቱን ጠቅሰው፣ ከዚህ ቀደም ምርት የማይሰጡ መሬቶች ምርት መስጠት መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ በክልሉ በተዳፋታማ አካባቢዎች የጠረጴዛማ እርከን በመስራት የአፈር ለምነትን ለመመለስ እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። በዘንድሮው ዓመት በ678 ነባርና አዲስ ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ በማከናወን ከ147ሺህ ሄክታር በላይ መሬት እንደሚለማ የተናገሩት ደግሞ የቢሮው ምክትልና ተፈጥሮ ሃብትና ደን ልማት ዘርፍ ሃላፊ አበባየሁ በየነ ናቸው፡፡ በቀጣይ ሳምንት በሚጀመረው የ2018 በጀት ዓመት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ ምርት የማይሰጡ ተራራማ ቦታዎችን በጠረጴዛማ እርከን ማልማት ሥራ ይከናወናል ብለዋል፡፡
በሚቀጥሉት አሥር ቀናት በአብዛኛው የኢትዮጵያ አካባቢዎች ደረቅና ቀዝቃዛ አየር ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jan 12, 2026 90
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አሥር ቀናት በአብዛኛው የኢትዮጵያ አካባቢዎች ደረቅና ቀዝቃዛ አየር ተጠናክሮ አንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፣በሚቀጥሉት አሰር ቀናት አብዛኞቹ የኢትዮጵያ ክፍሎች ደረቅና ቀዝቃዛ አየር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አሀዛዊ የትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ ብሏል። የበጋው ደረቅ ጸሃያማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ በአብዛኛው የሀገሪቱ ክፍሎች እንደሚስተዋልና የለሊትና የማለዳው ቅዝቃዛ ከአምስት ዲግሪ ሼልሲየስ በታች እንደሚሆን አመልክቷል። ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው የሆኑ የደቡብና የደቡብ ምስራቅ አካባቢዎችደረቅ ሆነው እንደሚቆዩም የትንበያ መረጃው ያመለክታል። በሌላ በኩል በደቡብ ምዕራብ፣የምዕራብና የመካከለኛው እንዲሁም ሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ አንጻራዊ የእርጥበት መጠንና የደመና ሽፋን ጥንካሬ ሊኖራቸው እንደሚችል በትንበያው ተመላክቷል።
በኦሮሚያ ክልል በ32 ሺህ የችግኝ ማፊያ ጣቢያዎች ችግኝ የማዘጋጀት ስራ እየተከናወነ ነው
Jan 12, 2026 128
አዳማ ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በ32 ሺህ የችግኝ ማፊያ ጣቢያዎች በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር የሚተከሉ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። በክልሉ ግብርና ቢሮ የደን ልማትና እንክብካቤ ዳይሬክተር አቶ ከተማ አብዲሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብርና የተፈጥሮ ልማትና ሀብት ስራ ለምርታማነት እንዲሁም ለአካባቢ ጥበቃ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተጎዱና የተራቆቱ መሬቶች እንዲያገግሙ፣ የደረቁ ኃይቆች፣ ወንዞችና ጅረቶች እንዲመለሱ ማድረጉንም ገልጸዋል። በተያዘው በጋ ወራትም በ32 ሺህ የችግኝ ማፊያ ጣቢያዎች ለኢኮኖሚ፣ ለምግብነት ፣ለደን ሽፋንና ለውበት የሚውሉ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ከችግኝ ማፊያ ጣቢያዎቹ ጎን ለጎን የክልሉ አርሶ አደሮችም በችግኝ ዝግጅቱ እየተሳተፉ መሆኑን ጠቁመዋል። በክልሉ ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር እየተዘጋጁ ካሉ ችግኞች ውስጥ ለፍራፍሬ፣ ለጥምር ደን አገልግሎት፣ ለአፈር ለምነትና ለውበት የሚውሉ 60 በመቶ ሲሸፍኑ ቀሪዎቹ 40 በመቶ ለደን ሽፋን አገልግሎት እንደሚውሉ ገልጸዋል። ባለፈው ክረምት ከተተከሉት ችግኞች ውስጥ በመጀመሪያው ዙር ቆጠራ ከ90 በመቶ በላይ መጽደቁንም ጠቁመዋል።
የተፈጥሮ ሀብትን በመጠበቅና በመንከባከብ የለማች ሀገር ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ ይገባል
Jan 12, 2026 105
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦የተፈጥሮ ሀብትን በመጠበቅ፣ በመንከባከብና በአግባቡ በመጠቀም የለማች ሀገር ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ የአሁኑ ትውልድ ሃላፊነት መሆኑ ተገለጸ። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ዘንድሮ የሚካሄደውን የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራን አስመልክቶ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥቷል። የቢሮው ሃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ እንደገለጹት፤ በክልሉ በዘንድሮው ዓመት 6 ሺህ 386 ተፋሰሶች ላይ 3 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር በሚሆነው መሬት ላይ የተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ ጥብቃና እንክብካቤ ሥራ ይከናወናል። "የአካባቢ ልማት፣ እንክብካቤና ጥበቃ ለሀገር ማንሰራራት" በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄደው የዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ከነገ ጥር 5 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለ60 ተከታታይ ቀናት የሚከናወን መሆኑንም አመልክተዋል። የተፈጥሮ ሀብትን በመጠበቅ፣ በመንከባከብና በአግባቡ በመጠቀም የለማች ሀገር ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ የአሁኑ ትውልድ ሃላፊነት እንደሆነ የገለጹት አቶ ጌቱ፤ ለልማት ስራው ስኬታማነት አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራ እና የባለሙያ ስልጠና መከናወኑን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት በክልሉ በተከናወኑት የተፋሰስ ልማትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የችግኝ ተከላ ስራዎች ክልሉ የነበረው የደን ሽፋን ማደጉን ገልጸዋል። በዚህም ደርቀው የነበሩ ምንጮችና ኩሬዎች እንዲያገግሙ እና በበርካታ አካባቢዎች ላይ የአየር ንብረትና የመሬት ስነ ምህዳር እንዲሻሻል ማድረጉን ተናግረዋል። በዚህም ቀድሞ ለእርሻ አመቺ ያልነበሩ መሬቶች ጭምር ለግብርና ሥራ እየዋሉ በመምጣታቸው በክልሉ ወጣቶችና አርሶ አደሮች ተደራጅተው በልዩ ልዩ የግብርና ስራዎች ላይ በመሰማራት ምርትና ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ውጤት እየታየ መምጣቱን አመልክተዋል። በበጋ ወራት የተፋሰስ ልማት በተከናወነባቸው ቦታዎች ላይ በክረምቱ ወራት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እንደሚተከሉ ገልጸው፤ ዘንድሮ በሚካሄደው የተፋሰስ ልማት ስራም የክልሉ ህዝብ በሙሉ አቅሙ በመሳተፍ ውጤታማ ስራ እንዲያከናውን አቶ ጌቱ ጥሪ አቅርበዋል። የዘንድሮው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና እንክብካቤ ስራ በኦሮሚያ ክልል ደረጃ በነገው እለት የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በተገኙበት በቡኖ በደሌ ዞን ይጀመራል።
በድሬደዋ አስተዳደር የበጋ ወራት የተፋሰስ ልማት ስራ ተጀመረ
Jan 11, 2026 193
ድሬደዋ፣ጥር 3/2018(ኢዜአ) ፡-በድሬደዋ አስተዳደር 38ቱ የገጠር ቀበሌዎች የበጋ ወራት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ዛሬ መካሄድ ጀመረ። በአስተዳደሩ አራቱ የገጠር ክላስተሮች ዛሬ በተጀመረውና ለአንድ ወር በሚዘልቀው የበጋ ወራት የተፋሰስ ልማት ሥራ 5ሺህ 550 ሄክታር የሚሸፍን የተፋሰስ ልማት እንደሚከናወን ታውቋል። በአሰሊሶ ገጠር ክላስተር ገንደ ሪጌ ቀበሌ ተገኝተው የተፋሰስ ልማቱን ያስጀመሩት የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር እና የአስተዳደሩ ምክርቤት ምክትል አፈጉባኤ ወይዘሮ ከሪማ አሊ ናቸው። የድሬደዋ አስተዳደር ምክርቤት አፈጉባኤ አቶ አብዲ ሙክታር፣ የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ፣ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የድሬደዋ አስተዳደር ምክርቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍና ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች በተቀሩት ክላስተሮች ተገኝተው የተፋሰስ ልማቱን አስጀምረዋል። "የተቀናጀ የበጋ ወራት የተፋሰስ ልማት፤ ለግብርና ሽግግር ስኬት" በሚል መሪ ሃሳብ በተጀመረው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ላይ የተለያዩ የአፈርና የውሃ ሃብትን በዘላቂነት መጠበቅና ማበልፀግ የሚያስችሉ ተግባራት እንደሚካሄዱም በወቅቱ ተገልጿል። ለአንድ ወር በሚካሄደው የተፋሰስ ልማት ስራው ከ37ሺህ 900 በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚሳተፉም ታውቋል።
በዞኑ በልዩ ትኩረት ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Jan 10, 2026 139
መቱ፤ ጥር 2/2018 (ኢዜአ)፡- በኢሉአባቦር ዞን በልዩ ትኩረት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የዞኑ የግብርና ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አወል መሐመድ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በያዝነው የበጋ ወራት በዋናነት የተቀናጀ የአፈርና ውኃ ጥበቃን ጨምሮ ችግኝ የማዘጋጀት ሥራ እየተሠራ ነው። በዚህም መሠረት 131 ሺህ ሔክታር መሬት የሚሸፍን የተፋሰስ ልማት ሥራ ሕብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። የተፋሰስ ልማት በተሠራባቸው አካባቢዎች የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው በርካታ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆናቸውንም ጠቁመዋል። ችግኞቹ ለምግብነት፣ ለደን ልማት፣ ለከብቶች መኖና ለውበት የሚውሉ መሆናቸውንም ነው ያብራሩት። የችግኝ ዝግጅቱ በመንግሥት ችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እና በአርሶ አደሮች ማሳ ላይ መካሄዱንም አስረድተዋል። በመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች ከአካባቢ ጥበቃ ፋይዳ ባለፈ በችግኝ ማፍላት ለሚሳተፉ ወገኖች የሥራ እድል እንደፈጠሩመ አክለዋል። በችግኝ ማፍላት ሥራው የሥራ እድል ከተፈጠረላችው መካከል ሽብሩ አምቢሳ እንዳሉት፤ በችግኝ ጣቢያዎች ተቀጥረው ከሚያገኙት ገቢ ባሻገር በሥራው ያገኙትን ልምድ በግል ማሳቸው ላይ ለማስፋት ማቀዳቸውን ተናግረዋል። ችግኞችን ከማዘጋጀት ሥራ ጎን ለጎን ባለፈው ክረምት የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ሥራም እያከናወኑ መሆናቸውን ነው የተናገሩት። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር መተግበር ከጀመረ ወዲህ ችግኝ በማዘጋጀት ገቢ እያገኙበት መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አበራ ገለታ ናቸው።
በሐረሪ ክልል በተፋሰስ ልማት የተከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ምርትና ምርታማነትን አሳድጓል
Jan 10, 2026 148
ሐረር፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል ባለፉት ዓመታት በተፋሰስ ልማት የተከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ምርትና ምርታማነት ማሳደጉን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር ገለጹ። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ሃላፊ ሮዛ ኡመር፤ የዘንድሮውን የክልሉን የተፋሰስ ልማት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በዛሬው እለት አስጀምረዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ተጨባጭ ውጤት የተገኘበት መሆኑን አንስተው ዘንድሮም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። በተለይም የከርሰ ምድር ውሃን በማጎልበትና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል። የክልሉ የተፈጥሮ ሀብት ልማት አጠቃቀም እና ጥበቃ ዳይሬክተር አራርሶ አደም፤ በክልሉ በዘንድሮ በጋ ወራት 9 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እንደሚከናወን ተናግረዋል። በዚህም 300 ሄክታር በሚሆን መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው እንደሚከናወን ጠቁመው በተፋሰስ ልማት ስራው ከ11 ሺህ በላይ ሰዎች ይሳተፋሉ ብለዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የለሙ ተፋሰሶች የጎርፍ ተጋላጭነትን ከመቀነስ ባለፈ ለወጣቶች የስራ ዕድል እንደፈጠረም ገልጸዋል።