ቀጥታ፡
አካባቢ ጥበቃ
የተፋሰስ ልማት ሥራ የመሬት ለምነትን በመጨመር ምርታማነትን አሳድጓል
Jan 23, 2026 143
ሃዋሳ፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ):-የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈር መሸርሸርን በማስቀረትና የመሬት ለምነትን በመጨመር ምርታማነታቸውን በማሳደጉ ልማቱን አጠናክረው መቀጠላቸውን የሲዳማ ክልል አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንዳሉት ቀደም ሲል በተፋሰስ ልማት ያከናወኗቸው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የአፈር መሸርሸርን በማስቅረትና የመሬት ለምነትን በመጨመር ምርትና ምርታማነታቸውን እያሳደገው ነው። ተጠቃሚነታቸውን አጠናክሮ ለማስቀጠልም በአሁኑ ወቅትም የተፋሰስ ልማት ስራ እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ከአርሶ አደሮቹ መካከል አቶ ቶማስ መራሳ እንደገለጹት በየዓመቱ በተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ በመሳተፍ የአካባቢያቸውን ለምነት እየጠበቁ ነው፡፡ ተፋሰስ ልማቱ ምርታማነትን በማሳደግ ተጠቃሚ እያደረጋቸው በመምጣቱ በአሁኑ ወቅትም በቡድን ተደራጅተው ልማቱን እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ተከናውኖ ባገገሙ መሬቶችም ቡናና ፍራፍሬዎችን በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ሌላው አርሶ አደር ጴጥሮስ ሶቾሳ በበኩላቸው በተፋሰስ ልማት ሥራው አርሶ አደሩ በንቃት እየተሳተፈና ተጠቃሚነቱን እያረጋገጠ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በአካባቢያቸው ከዚህ ቀደም ገላጣ የነበሩና የተጎዱ መሬቶች ማገገማቸውን ጠቅሰው፣ በእርሻ ማሳቸው የነበረውን ባህር ዛፍም በመንቀል የመሬታቸውን ለምነት እየጠበቁና ምርታማነት እያሳደጉ መምጣታቸውን ተናግረዋል። የተፋሰስ ልማት ሥራው ምርት የማይሰጡ መሬቶች ወደ ምርት እንዲገቡና የሥራ እድል እንዲፈጠር ማድረጉን የገለጹት ደግሞ ሌላው አርሶ አደር ሳሙኤል ጢሞቲዮስ ናቸው። ቀበሌያቸው ተዳፋታማ በመሆኑ ጎርፍ መሬታቸውን በመሸርሸር ለምነቱን እያጣ በመምጣቱ ከልማቱ ተጠቃሚ ሳይሆኑ መቆየታቸውን አስታውሰው፣ የተፋሰስ ልማት ሥራ ከተጀመረ ወዲህ በየዓመቱ ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል።   የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው በክልሉ በየዓመቱ የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የተጎዳ መሬት እንዲያገግም ጉልህ አስተዋጾ እያደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። የውሃ አማራጮችን በመጨመር የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ጉልህ ሚና በመጫወታቸው ልማቱ በየዓመቱ እየተጠናከረ መምጣቱንም ገልጸዋል። በዚህም በክልሉ በየጊዜው በሚካሄዱ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ የሚሳተፉ አርሶ አደሮች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በክልሉ በዘንድሮ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ ከ147 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚለማ ሲሆን በተለዩ 678 ንኡስ ተፋሰሶች ለ30 ተከታታይ ቀናት የሚቆይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እንደሚከናወን ታውቋል።
ኢትዮጵያ በውኃ ሀብት አስተዳደር እና በተፋሰስ ልማት ሥራዎች ውጤታማ ተግባራት እያከናወነች ነው 
Jan 22, 2026 106
ነቀምቴ ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በውኃ ሀብት አስተዳደርና በተፋሰስ ልማት ሥራዎች ውጤታማ ተግባራት እያከናወነች መሆኑን የውኃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት እቅድ አፈጻጸም ግምገማ በነቀምቴ ከተማ እየተካሄደ ነው።   የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር)፣ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ባለፉት ዓመታት የውኃ ሀብትን በአግባቡ አልምቶ ጥቅም ላይ ለማዋል የተወሰዱ እርምጃዎች ውጤት እያስገኙ ነው። ኢትዮጵያ የምትከተለው ፍትሃዊና ምክንያታዊ የውኃ ሀብት አጠቃቀምና አስተዳደርም የልማት እንቅስቃሴን ለማፋጠን ጉልህ ሚና አለው ብለዋል። ኢትዮጵያ በውኃ ሀብት አስተዳደርና በተፋሰስ ልማት ስራዎች እየከናወነች ያለው ሥራ ተጨባጭ ውጤት ማምጣቱን በመግለጽ። በሌላ በኩል ሚኒስቴሩ በተፋሰስ ልማትና በቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ስራዎች ተስፋ ሰጪ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን አንስተዋል። ከውሃ ሀብት በተጨማሪ የኢነርጂ ሀብትን በአግባቡ መለየትና ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባም አንስተዋል።   በመድረኩ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የፌዴራልና የክልሎች እንዲሁም ሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች የውሃ እና ኢነርጂ ቢሮ ሀላፊዎች ተሳትፈዋል።
የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ጥቅምን በተግባር ስላየነው አጠናክረን እንቀጥላለን - አርሶአደሮች
Jan 22, 2026 183
አሶሳ፤ ጥር 14/2018 (ኢዜአ)፦ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ጥቅምን በተግባር በማየታቸው ተግባሩን አጠናክረው መቀጠላቸውን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የቡልድግሉ ወረዳ አርሶአደሮች ተናገሩ። በምዕራብ ወለጋ ዞን በ 487 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው የተፋሰስ ልማት የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ መሰረት ሆኗል- ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ   አርሶአደ ሂድር ኡስማን እንዳሉት፤ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ዘላቂ የመሬት አያያዝና አጠቃቀም እንዲኖር ከማድረግ በተጨማሪ የአካባቢውን የአየር ንብረት በማስተካከል ሚናው የጎላ ነው።   ወይዘሮ ማርታ ዋቅቶላ በበኩላቸው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ መሠራት ከጀመረ ወዲህ በጎርፍ የሚወሰደው ለም አፈር በመቀነሱ ምርታማነታቸው እንዲጨምርና የአካባቢው ሥነ-ምኅዳርም መጠበቁን ተናግረዋል። የተፈጥሮ ፀጋን የማልማትና የመጠበቅ ስራው ተጠናክሮ ይቀጥላል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ   ከዚህ በፊት የተከናወነው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ የተራቆቱ አካባቢዎች መልሰው እንዲያገግሙ በማድረግ በደን እንዲሸፈኑ ማስቻሉን ያስረዱት ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጭ ቢራቱ ፉፋ ናቸው። ቀደም ሲል ከተሠራው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ተጠቃሚነታቸውን ገልጸው፤ በቀጣይም አካባቢን ጠብቆ ለትውልድ የማስተላለፍ ተግባር ስለሆነ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ ገልጸዋል።   የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትልና የተፈጥሮ ሀብት ልማት ዘርፍ ኃላፊ አብዱልከሪም ሙሳ፤ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ የአካባቢውን ሥነ-ምኅዳር ይጠብቃል፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብም በደለል እንዳይሞላ ይረዳል ብለዋል። ስለዚህ አርሶአደሩ ተሳትፎውን አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አሳስበዋል። ዘንድሮው በክልሉ ከ57 ሺህ ሔክታር በላይ ማሳ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ለማከናወን መታቀዱን አውስተዋል።
በምዕራብ ወለጋ ዞን በ 487 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ  ነው
Jan 22, 2026 126
ጊምቢ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ወለጋ ዞን በ487 ተፋሰሶች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ በምዕራብ ወለጋ ዞን ግብርና በጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ፍቅሩ ብርሃኑ እንዳሉት፣ በዞኑ በ487 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ ነው፡፡   ባለፉት አመታት በዞኑ በተከናወኑ የተለያዩ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች በመጡ ተጨባጭ ለውጦች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ በማድረጋቸው ለዘንድሮ ተፋሰስ ልማት ስራዎች በነቂስ ወጥተው እየተሳተፉ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል፡፡ በዞኑ ከ273 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚሸፍን የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ መካሄድ ጀምሯል በተለይም እየተከናወኑ ባሉ የተፋሰስ ልማት ስራዎች የእርከን ስራና ቀደም ብለው የለሙ ተፋሰሶች ከእንስሳትና ከሰው ንክኪ ነጻ እንዲሆኑ ጥበቃ ይደረግለታል ብለዋል።   በዞኑ በላሎሳቢ፣ በመነስቡ፣ በጊምቢና ሆማ ወረዳዎች በእስካሁኑ እንቅስቃሴ በእርከን ስራ የተሻለ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት በተፋሰስ ልማት መርሃ ግብር በተከናወኑት ስራዎች የተራቆቱ አካባቢዎች ወደ ልምላሜ መመለሳቸውን እና በዘንድሮው የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ላይ በንቃት እንዲሳተፉ ምክንያት እንደሆናቸው የሚናገሩት ደግሞ አርሶ አደር አምቢሳ ጉዲና ናቸው፡፡   ልማቱ ቀደም ሲል በአፈር መሸርሸር ምክንያት ምርታማነት ቀንሶ የነበረው የእርሻ መሬታቸው አሁን ላይ ማገገሙን ጠቅሰዋል። አርሶ አደር ከኔሳ አሙማ በበኩላቸው፤ ባለፉት አመታት በተከናወኑት የእርከንና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች በአካባቢያቸው ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡   በመሆኑም በዘንድሮ የበጋ ወራት የእርከን ልማት ስራዎች ላይ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የተፋሰስ ልማት የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ መሰረት ሆኗል- ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ
Jan 21, 2026 153
ሀዋሳ፣ጥር 13/2018 (ኢዜአ):-በሲዳማ ክልል የተፋሰስ ልማት ሥራ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ መሰረት መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ክልል አቀፉን የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ በሰሜናዊ ሲዳማ ዞን ሀዌላ ወረዳ ዱለቻ ጠዌራኮ ቀበሌ አስጀምረዋል።   አቶ ደስታ ሌዳሞ በዚህ ወቅት እንደገለጹት በክልሉ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የአፈር ለምነትን በመጠበቅ ምርታማነት እንዲጨምር አድርጓል። የተፋሰስ ልማት ሥራው የተጎዳ መሬት እንዲያገግም በማድረግ የአፈር ለምነትን ከመጠበቅ ባሻገር ለወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር ለገቢ ምንጭ እየሆነ መምጣቱንም ገልጸዋል። ከዚህ ቀደም በጎርፍ ምክንያት የአፈር መሸርሸር ሲከሰት እንደነበር አስታውሰው፣ በተፋሰስ ልማት ሥራው በለሙ አካባቢዎች የእንስሳት መኖን ጨምሮ የተለያዩ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በተፋሰስ ልማት ሥራው የተገኙ ውጤታማ ሥራዎችን በማስቀጠል አረንጓዴና ለኑሮ ምቹ ስነምህዳር የመፍጠር ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፋኖሴ መኮንን በበኩላቸው፣ ባለፉት ዓመታት እንደሃገር በተከናወነ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ 33 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚጠጋ መሬት መልማቱን ተናግረዋል፡፡   በዚህም የአፈር ለምነትን በመጠበቅ የግብርና ምርታማነትን የማሳደግ፣ የውሃ አማራጮችን የማስፋትና በለሙ ተፋሰሶች የስራ ዕድል በመፍጠር ወጣቶችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ በሲዳማ ክልል በ2018 በተለዩ 678 ንኡስ ተፋሰሶች የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በማከናወን ከ147 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን የገለጹት ደግሞ የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ ናቸው። ለአንድ ወር በሚቆየው የተፋስስ ልማት ሥራ ተዳፋታማ በሆነ አካባቢዎች ለሚከናወን የጠረጴዛማ እርከን ስራና በእርሻ ማሳ ውስጥ ያለውን ባህር ዛፍ በመንቀል በትኩረት እንደሚከናወን ተናግረዋል፡፡   ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ ሥራዎች የአፈር መከላትን መቀነስ፣ የውሃ አማራጮችን የማስፋትና ምርት የማይሰጡ አካባቢዎችን ወደ ምርት በማስገባት ዓመታዊ የሰብል መሬት ሽፋን ለማሳደግ መሰራቱን ገልጸዋል። በቀበሌው ከዚህ ቀደም በለማ ተፋሰስ የሥራ እድል ከተፈጠረላቸው ወጣቶች መካከል ወጣት እንድሪያስ ኢዩኤልና ሰለሞን ዳንኤል በተፋስስ ልማት በለሙ አካባቢዎች የሥራ እድል እንደተፈጠረላቸው ተናግረዋል፡፡ በአካባቢው በለማ ተፋሰስ ላይ ለአምስት ተደራጅተው በመንግስት በተመቻቸላቸው የገንዘብ ብድር በንብ በማነብ ሥራ ተሰማርተው ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡   በመርሃግብሩ ላይ የሲዳማ ክልል አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ሥራ ሃላፊዎች፣ የሃገር ሽማግሌዎችና የተለያዩ የህብረተሰብ ከፍሎች ተሳትፈዋል፡፡ በዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ሥራ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ይሳተፋል ተብሏል።  
የተፈጥሮ ፀጋን የማልማትና የመጠበቅ ስራው ተጠናክሮ ይቀጥላል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Jan 21, 2026 177
ካራት፤ ጥር 13/2018 (ኢዜአ):- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተፈጥሮ ፀጋን በማልማትና በመጠበቅ ለትውልድ ምቹ ሥነ ምህዳር ለማውረስ የተጀመረው ሥራ እንደሚጠናከር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ክልል አቀፍ የ2018 በጀት ዓመት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማትና የበልግ አዝመራ ንቅናቄ መርሃ ግብር ዛሬ በኮንሶ ዞን በይፋ ተጀምሯል።   የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ በማስጀመሪያ መርሃ-ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት የክልሉን የተፈጥሮ ፀጋ በማልማት ለትውልዱ ምቹ ስነ ምህዳር ለማውረስ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ እየተከናወነ ነው። ባለፉት ዓመታት በቅንጅት በተሰሩ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ሥራዎችም ምርትና ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ የተራቆቱ ተራራዎችን በማልማት ከስጋት ወደ ሀብት ምንጭነት ለመለወጥ መቻሉን ተናግረዋል። በዘንድሮ የተፋሰስ ልማት ሥራም የኮንሶዎችን የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ባህልን በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች ለማስፋፋት ልዩ ትኩረት መሰጠቱንም ርዕሰ መስተዳድሩ ጠቁመዋል። በክልሉ ያለውን የተፈጥሮ ሀብት በማልማትና በመጠበቅ ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ ለትውልዱ ምቹ ሥነ ምህዳር ለማውረስ የተጀመረው ሥራ በቀጣይም ይጠናከራል ብለዋል።   በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) የዘንድሮው የተፋሰስ ልማት በ159 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ እንደሚከናወን ገልጸዋል። በዚህም 1ሺህ 384 የተለያዩ ቦታዎች ላይ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ እንደሚከናወን ጠቁመዋል። በተፋሰስ የለሙ አካባቢዎችን በስነአካላዊና ስነ ህይወታዊ ሥራዎች ፍራፍሬና የእንስሳት መኖ በማልማት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የተጀመረውን ጉዞ ለማሳካት ይሰራል ሲሉም አመልክተዋል። እንደኃላፊው ገለጻ በክልሉ ባለፉት ስድስት ዓመታት የተፋሰስ ልማት ሥራ በተከናወነባቸው አካባቢዎች ከ164 ሺህ በላይ ዜጎች የሥራ ዕድል ተፈጥሮላቸዋል።   የኮንሶ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ገሌቦ ጎልቶሞ በበኩላቸው በዞኑ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራው የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት እያሳደገው መምጣቱን ነው የተናገሩት። ኮንሶዎች ከ500 ዓመታት በፊት የጀመሩት የእርከን ሥራ ለምርትና ምርታማነት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም አመልክተዋል። በዞኑ የተፈጥሮ ሀብቶችን በማልማት፣ በመንከባከብና በአግባቡ በመጠቀም የግብርና ትራንስፎርሜሽንን ለማረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ መሆኑንም አስታውቀዋል።   የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ ባህልን በማሳደግ ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ የበኩላችንን እየተወጣን እንገኛለን ያሉት ደግሞ የኮንሶ ዞን አርሶ አደር ካፖሌ ገድሻ ናቸው። በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ለአንድ ወር በሚካሄደው የተፋሰስ ልማት ሥራ ከ2 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል። በተፋሰስ ልማትና የበልግ አዝመራ ንቅናቄ መርሃ ግብር ላይ የክልሉና የዞን ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች፣ የኮንሶ ዞን ነዋሪዎችና ሌሎችም ተሳትፈዋል።      
የተፋሰስ ልማት ሥራ ለምርታማነት መጨመር ከፍተኛ እገዛ አድርጓል 
Jan 20, 2026 225
መቱ፤ ጥር 12/2018 (ኢዜአ)፡- የተፋሰስ ልማት ሥራ ለምርታማነት መጨመርና ለተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ከፍተኛ እገዛ ማድረጉን የቡኖ በደሌና የኢሉባቦር ዞኖች አርሶ አደሮች ተናገሩ። በቡኖ በደሌ ዞን የዳቦ ሐና ወረዳ ነዋሪዎች አርሶ አደር ዲንቃ ገቢ እና ታሪኩ አብዲሳ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ምርታማነት እንዲጨምር ከፍተኛ እገዛ አድርጓል።   በተጨማሪም እየተመናመኑ የነበሩ የደንና የውኃ ሀብቶች እንዲመለሱ ማድረጉን ተናግረዋል። የተፋሰስ ልማት ሥራ የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙና ምርታማነታቸው እንዲጨምር ማድረጉን የተናገሩት ደግሞ በኢሉአባቦር ዞን የሁሩሙ ወረዳ ነዋሪ አርሶአደሮች ተካልኝ ታደገ እና ዓለማየሁ በቀለ ናቸው። የተፋስ ልማት የተከናወነባቸው አካባቢዎችን ከሰውና ከእንስሳት ንኪኪ በመጠበቅ ለመኖ ልማት ብሎም ለንብ ማነብ ሥራ እያዋሏቸው መሆኑንም ጠቁመዋል። ቀደም ሲል ከተከናወነ የተፋሰስ ልማት የተገኘውን ተጠቃሚነት በመገንዘብ፤ በቀጣይም ሥራውን በባለቤትነት አጠናክረው ለማስቀጠል ቁርጠኛ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።   የቡኖ በደሌ ዞን ዋና አሥተዳዳሪ አማን ደኑ በበኩላቸው፤ የተፋሰስ ልማት ሥራ በአርሶ አደሩ ዘንድ መደበኛ ተግባር ሆኖ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል። የዓየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመከላከል፣ ምርታማነትን ለማሳደግና የተፈጥሮ ሀብትን ለመጠበቅ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ወሳኝ ነው ያሉት ደግሞ የኢሉአባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ቻላቸው አዱኛ ናቸው። ለሁለት ወራት የሚቆይ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ በዞኖቹ በ479 ተፋሰሶች ላይ እየተከናወነ ይገኛል።
በአስተዳደሩ የተከናወነው የተፋሰስ ልማት ስራ አርሶ አደሮች ከተረጂነት እንዲወጡ አስችሏል
Jan 16, 2026 133
ድሬዳዋ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡-በድሬዳዋ አስተዳደር ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች ከተረጂነት ለመውጣት እንዳስቻላቸው አርሶአደሮች ተናገሩ። በተፋሰሱ እና በሌሎች የገጠር ልማቶች በተከናወነው ስራ በመታገዝ ዘንድሮ ከ38 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ከተረጂነት ወደ አምራችነት እንደሚሸጋገሩ አስተዳደሩ አስታውቋል ።   ባለፉት ዓመታት የተሰሩት ልማቶች የተፈጥሮ ሃብት ይዞታን በመመለስ፣ የጎርፍ ችግርን በመከላከልና ምንጮችን በመመለስ ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ማስቻሉን ዘንድሮ በተጀመረው የተፋሰስ ልማት እየተሳተፉ የሚገኙ አርሶአደሮች ለኢዜአ ገልጸዋል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል የገንደ ሪጌ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ሱልጣን ፈጃል እንደገለፁት፤ ተፋሰሱ ተጨማሪ የእርሻ መሬትና ውሃን እንዲጠቀሙ በማስቻሉ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ተሰማርተው ህይወታቸውን ለመለወጥ አስችሏቸዋል።   ቀደም ብለው ዓልምተው የነበረው ብርቱካን ባለፈው ሳምንት ተሰብስቦ ከ900 ሺህ ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን እንደአብነት አንስተዋል። ከብርቱካን በተጨማሪ ሽንኩርት፣ ሃባብና ሎሚ እያመረቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። .የኡሉል ሞጆ ቀበሌ አርሶአደር ወይዘሮ ሐሊማ መሐመድ በበኩላቸው፣የተፋሰስ ልማቱ ለግብርና ስራ ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩ አርሶአደሩ በምንጭና በዝናብ ውሃ በዓመት ከሁለት ጊዜ በላይ እያመረተ መሆኑን ተናግረዋል።   ይሄን የመሰለ የተፈጥሮ ፀጋና ጉልበት እያለን ለልመና እጅ አንዘረጋም ያሉት አርሶአደር ሐሊማ፤ ከራሳችን አልፈን ለተቸገሩ ለመርዳት ጠንክረን እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። በተፋሰስ ልማትና በሌማት ትሩፋት በተፈጠሩላቸው እድሎችና ድጋፎች በመታገዝ ከተረጂነት ወደ አምራችነት በመሸጋገር ከልማታዊ ሴፍትኔት መውጣታቸውን የገለፁት ደግሞ ሌላው የኡሉል ሞጆ ቀበሌ አርሶአደር ኡስማን መሐመድ ናቸው።   የቀበሌው ህብረተሰብ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት የመሸጋገርን መርህ ለማሳካት በተፋሰስ ልማትንም ሆነ በሌሎች ስራዎች እየተጋ መሆኑን አንስተዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኑረዲን አብደላ፤ ባለፉት ዓመታት በድሬዳዋ የገጠር ቀበሌዎች በሚገኙ 57 ሺህ ሄክታር የተራቆቱ ተፋሰሶች ላይ የተለያዩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል።   በተከናወኑት ተግባራት ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ በአነስተኛ መስኖ ልማት በመሰማራት አበረታች ውጤት መገኘቱን የገንደ ሪጌ ገጠርን በአብነት ጠቅሰው አስረድተዋል። እንደ ኃላፊው አቶ ኑረዲን ገለፃ እየተከናወኑ የሚገኙ አበረታች የገጠር ልማቶች ከተረጂነት ወደ አምራችነት የመሸጋገሩን ጉዞ ስኬታማ ያደርጉታል። በዘንድሮ በጀት አመት 38 ሺህ በልማታዊ ሴፍትኔት የታቀፉ አርሶአደሮችና አርብቶአደሮች ወደ አምራችነት ይሸጋገራሉ ብለዋል።
በዞኑ የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በ631 ተፋሰሶች ላይ እየተካሄደ  ነው
Jan 16, 2026 129
ወልዲያ ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡-በሰሜን ወሎ ዞን የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በ631 ተፋሰሶች ላይ እየተካሄደ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የተፈጥሮ ሃብት ባለሙያ አቶ ጋሻው አለሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ባለፉት አመታት የተከናወነው የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ደርቀው የነበሩ ምንጮች እንደገና በመፍለቃቸውና የከርሰ ምድርና ገጸ-ምድር የውሃ አቅም በመጨመሩ አርሶ አደሩ በስራው በንቃት እንዲሳተፍ አድርጓል። የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአፈር ለምነትን በማሳደጉና የውሀ አማራጮች መስፋታቸው ለመስኖ ልማት ስራው ስኬት ተጨማሪ አቅም መፍጠራቸውን ገልጸዋል።   ስራዎቹ ተራቁተው የነበሩ ተራሮችን ወደ ልምላሜ በመመለሳቸው አርሶ አደሩ በመኖ ልማትና በንብ ማነብ ስራ በመሰማራት ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እንዳስቻለው ተናግረዋል። በዘንድሮው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ 380 ሺህ 493 አርሶ አደሮች 631 ተፋሰሶችን እያለሙ መሆኑን አስረድተዋል። በዘንድሮው የአፈርና ውሃ እቀባ ልማት ስራም 443 ሺህ 77 ሄክታር መሬት ላይ የማሳና የተራራ ላይ እርከንና ሌሎች ስነ አካላዊ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዞኑ የመቄት ወረዳ የ029 ቀበሌ ነዋሪ አቶ አባቡ ዋለልኝ፣ ባለፉት ዓመታት ከተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ያገኘናቸውን ጥቅሞች ዘንድሮም ለማስቀጠል በትጋት እየሠራን ነው ብለዋል። ባለፉት ዓመታት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች አካባቢዎች አገግመው ለእንስሳት መኖ፣ ንብ ማነብና ሌሎች ስራዎች ጥቅም በመስጠታቸው ዘንድሮ በራሳቸው ተነሳሽነት ለስራ መውጣታቸውን ተናግረዋል።   ባለፉት አምስትና ስድስት ዓመታት ባከናወኗቸው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች ዘርፈ-ብዙ ጥቅሞችን አግኝተንበታል ያሉን ደግሞ በላስታ ወረዳ የጠልፈጢት ቀበሌ ነዋሪ አቶ ታደሰ ዳምጤ ናቸው። በዚህም በጓሮአቸው በአነስተኛ መስኖ አትክልት በማልማት፣ መኖ በማጨድ በእንስሳት እርባታና ማድለብ ስራ በመሰማራት ተጨማሪ ሃብት ለማፍራት እንዳስቻላቸው አስረድተዋል። በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተሰራው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራ የዞኑን የደን ሽፋን ከ20 በመቶ በላይ ማድረሱን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በአካባቢ ጥበቃ ልማት የተሠሩ ሥራዎች ጤናማ ትውልድ ለማፍራት ከፍተኛ ፋይዳ አላቸው
Jan 16, 2026 124
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃና አረንጓዴ ልማት የተሠሩ ሥራዎች ጤናማ ትውልድ ለማፍራት የጎላ ፋይዳ እንዳላቸው በዓለም አቀፍ የጤና ተቋማት የሚሠሩ የጤና ባለሙያዎች ገለጹ።   የኢትዮጵያ የሕጻናት ሄማቶሎጂና ኦንኮሎጂ ማኅበር የምሥረታ መርሐ-ግብር በአዲስ አበባ ተካሂዷል። በመርሐ-ግብሩ የተሳተፉ የጤና ባለሙያዎች ለኢዜአ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የተከናወኑ የአካባቢ ጥበቃና የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች ጤናን ለመጠበቅ፣ ለስፖርታዊ እንቅስቃሴ እና ለማኅበራዊ ግንኙነቶች ያላቸው ፋይዳ ከፍተኛ ነው።   በአውስትራሊያ የጤና ባለሙያ የሆኑት ብሮንዊን ማክናማራ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ ከተማ በአካባቢ ንጽህና፣ አረንጓዴ ቦታዎችና ፓርኮችን በማስፋፋት ረገድ ከዚህ ቀደም ከሚያውቁት የተለየ ለውጥ ማየታቸውን ተናግረዋል። የፕላስቲክና የኬሚካል ውጤቶች የጤና ጉዳት የሚያስከትሉ በመሆኑ ብክለትን ለመከላከል እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችንም አድንቀዋል።   የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ለጤና አጠባበቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ያስረዱት ደግሞ የቶሮንቶ ዩንቨርሲቲ ፕሮፌሰር ሺላ ዋይትዝማን ናቸው። አረንጓዴና ንጹህ አካባቢ ጤናን ለመጠበቅ ከሚያስችሉ ጉዳዮች አንዱ መሆኑን ገልጸው፤ በሽታን አስቀድሞ መከላከል ከማከም የተሻለ ነው ብለዋል።   በ’ፒውር ኧርዝ’ የምሥራቅ አፍሪካ ዳይሬክተር ፍሬው ከፍያለው በአካባቢ ጥበቃ ተሟጋችነትና ወጣቶችን በማሳተፍ የጽዳት ሥራዎች ላይ ለበርካታ ዓመታት እየሠሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል።
በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ምርትና ምርታማነትን አሳድጓል
Jan 15, 2026 221
ሮቤ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦በባሌ ዞን ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ አስተዋጽኦ ማበርከቱን የዞኑ አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ የ2018 የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በጎሮ ወረዳ ወልተኢ ጨፋ ቀበሌ ደራርቱ ተፋሰስ ላይ ዛሬ ተጀምሯል።   ከወረዳው አርሶ አደሮች መካከል አህመድ መሐመድ እንዳሉት፤ ባለፉት ዓመታት በአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ የተራቆቱ መሬቶች መልማታቸው የንብ ማነብ ሥራን ለማከናወንና ምርታማነትን ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ ፈጥሮላቸዋል።   በዘንድሮ የበጋ ወቅትም ከአምናው የተሻለ የልማት ሥራ ለማከናወን ከአካባቢያቸው አርሶ አደሮች ጋር በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን አመልክተዋል። በተፋሰስ ልማት ስራ የአካባቢ መራቆትን ከመከላከል ባለፈ ደርቀው የነበሩ ምንጮች መልሰው መመንጨት ጀምረዋል ያሉት ደግሞ አርሶ አደር ሀሰን አብዶ ናቸው።   ከዚህ ቀደም በለሙ ተፋሰሶች ውስጥ የተተከሉ እጽዋቶች በመጽደቃቸውና እርጥበታማ አየር እንዲኖር በማስቻሉ የግብርና ስራን በተሻለ መልኩ በማከናወን ድርቅን ለመቋቋም እያገዛቸው መሆኑን ነው የተናገሩት። አርሶ አደር ሐምዛ ቃዲ በበኩላቸው እንዳሉት ባለፉት ዓመታት በተፋሰስ ልማት ሥራ በተሰሩ ሥራዎች ከምርት ውጭ ሆኖ የነበረ የእርሻ መሬታቸው በማገገሙ እስከ 40 ኩንታል የስንዴ ምርት ማግኘት ችለዋል።   አርሶ አደሮቹ እንዳሉት የተፋጥሮ ኃብት ጥበቃና የእንክብካቤ ሥራን በማጠናከር ምርታማነታቸውን ይበልጥ ለማሳደግ የጀመሩትን ሥራ አጠናክረው ይቀጥላሉ። የጎሮ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ እሸቱ ተክሌ በበኩላቸው፣ በወረዳው ባለፉት ዓመታት በቅንጅት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የአካባቢውን አየር ንብረት ከማስተካከል ባሻገር ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል ምንጭ መሆኑን ተናግረዋል።   በዞኑ ባለፉት ዓመታት በተከናወነ የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈር ለምነት በመጨመሩ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን የገለጹት ደግሞ የባሌ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሙአዊያ ፉአድ ናቸው፡፡   በዘንድሮው የበጋ ወራትም ሥራውን በተቀናጀ መንገድ አጠናክሮ በማስቀጠል የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ከ549 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ያሳተፈ ሥራ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡ ዘንድሮ በሚካሄደው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማትም በ166 ተፋሰሶች ላይ ከ84 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ ስነ አካላዊ ስራዎች ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል።   በመርሐግብሩ ላይ የተገኙት የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ተወካይ አቶ ሴይፋዲን ሀሰን፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ምርታማነትን ለማሳደግ ከሚያበረክተው ጠቀሜታ በተጨማሪ ለቀጣዩ ትውልድ የለማና አረንጓዴ ሀገርን የማስረከብ ዓላማ ያለው በመሆኑ ስራው ተጠናክሮ እንዲቀጥል ድጋፍና ክትትል ይደረጋል ብለዋል።
በክልሉ የተፋሰስ ልማት ውጤትን በማስቀጠል የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል - ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር)
Jan 15, 2026 126
ሾኔ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተፋሰስ ልማት ውጤትን አጠናክሮ በማስቀጠል የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የክልሉ የ2018 የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ማስጀመሪያ መርሃ ግብር በሀዲያ ዞን ምስራቅ ባዳዋቾ ወረዳ አምቡርሴ አንጁሎ ቀበሌ በአንጁሎ ንዑስ ተፋሰስ ላይ ተጀምሯል።   ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር) መርሃ ግብሩን ባስጀመሩበት ወቅት እንደተናገሩት በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወነ የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈርን ለምነት በመጨመሩ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ተችሏል፡፡ ዘንድሮው በበጋ ወራትም ሥራውን በተቀናጀ መንገድ በማስቀጠል የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ አርሶ አደሮችን ያሳተፈ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊና የገጠር ክላስተር አስተባባሪ ኡስማን ሱሩር በበኩላቸው ያለፉት ዓመታት የተፋሰስ ልማት ሥራዎች በክልል ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እያገዙ ነው።   በዚህም በ2015 የምርት ዘመን 142 ሚሊየን ኩንታል የነበረው ክልላዊ የምርት መጠን በ2017 ወደ 159 ሚሊየን ኩንታል በማደጉ ገበያም ማረጋጋት የሚያስችል አቅም ተፈጥሯል ብለዋል። በተራቆቱ አካባቢዎች የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የእንስሳት መኖ ልማትን በማሳደግ የወተት ምርታማነትን በተመሳሳይ ዓመት ከነበረበት 321 ሚሊየን ሊትር ወደ 675 ሚሊየን ሊትር ማሳደጉን ተናግረዋል፡፡ ተግባሩን በማስቀጠል በዘንድሮ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማትም በ1ሺህ 294 ንዑስ ተፋሰሶች ላይ ከ290 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል።
በዞኑ ከ273 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚሸፍን የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ መካሄድ ጀምሯል
Jan 14, 2026 256
አምቦ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሸዋ ዞን ከ273 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚሸፍን የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ መካሄድ መጀመሩን የዞኑ አስተዳደር ገለጸ። በዞን ደረጃ የሚካሄደው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በአምቦ ወረዳ ኢላሙ ጎሮምቲ ቀበሌ በይፋ ተጀምሯል። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የልማትና የዕድገት ግቦችን ለማሳካት እያገዘ ነው የምዕራብ ሸዋ ዞን ምክትል አስተዳደሪ አቶ አበበ ጨመዳ በወቅቱ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት አመታት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአፈር ለምነት እንዲመለስ አድርጓል።   በዚህ የበጋ ወራትም ተግባሩን በማስቀጠል ለሁለት ወራት የሚቆይ የተቀናጀ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ዘመቻ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ ከ273 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ እንደሚከናወን ተናግረዋል፡፡ በዘመቻ መልክ በሚካሄደው በዚህ ስራ ከ600 ሺህ በላይ የዞኑ ነዋሪዎች ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም አስረድተዋል።   የምዕራብ ሸዋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብዲሳ ሀይሉ በበኩላቸው፤ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራውን ውጤታማ ለማድረግ በየደረጃው ላሉ የግብርና ባለሙያዎች፣ ለአርሶ አደሮች እና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ስልጠና መሰጠቱን ተናግረዋል፡፡   የአምቦ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መሰረት ጉዲሳ እንዳሉት፤ ባለፉት ጊዜያት በወረዳው በተከናወኑት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ከልማት ወጪ የነበሩ አካባቢዎች ዳግም ወደ ልማት ገብተዋል።   ህብረተሰቡም ጥቅሙን በመረዳቱ በተፋሰስ ልማቱ በነቂስ ወጥቶ እየተሳተፈ መሆኑን ጠቅሰው በወረዳው ከ2 ሺህ 700 ኪሎ ሜትር መሬት በላይ የእርከን፣ የስነ-ህይወታዊና የስነ-አካላዊ ስራዎች ይከናወናል ብለዋል። የአምቦ ወረዳ ኢላሙ ጎሮምቲ ቀበሌ አርሶ አደሮች የተፋሰስ ልማት ስራው ተግባራዊ ከመሆኑ በፊት የእርሻ ማሳቸው ለም አፈር በጎርፍ በመጠረጉ ምርታማነታቸው መቀነሱን ጠቁመዋል።   ችግሩን ለማቅረፍም በየአመቱ በሚከናወነው የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መሳተፋቸውን አስረድተዋል። በተፋሰስ ልማቱ ባለፉት ዓመታት የተሰሩ አፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአፈር መሸርሸርን አስቀርቷል ብለዋል።ይህም የሰብል ምርታቸው እንዲጨምር ማድረጉን ተናግረዋል።
በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የተፋሰስ ልማት ስራ ተጨባጭ ውጤት አምጥቷል
Jan 13, 2026 189
ግራዋ ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የተፋሰስ ልማት ስራ ተጨባጭ ውጤት ማምጣቱ ተገለጸ። በዞኑ የዘንድሮ በጋ ተፋሰስ ልማት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የዞን ደረጃ በግራዋ ወረዳ በሜይራ ጉዲና መንደር ተጀምሯል።   በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የምስራቅ ሐረርጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ሚስኪ መሀመድ፤ በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የተፋሰስ ልማት ስራ አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ ለምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ አድርጓል ብለዋል።   በተለይም ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ አንጻር የተፋሰስ ልማት ስራ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አብራርተዋል። የኦሮሚያ ክልል መሬት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ መሰርት አሰፋ በበኩላቸው፤ የሐረርጌ አርሶ አደሮች በተፋሰስ ልማት ባገኙት ውጤት አካባቢያቸውን መቀየር መቻላቸውን አንስተዋል።   በዞኑ ተጎሳቅሎ የነበሩ አካባቢዎችን መልክአ ምድር በመጠበቅና የአፈር ለምነትን በማሻሻል አረንጓዴ መላበሱን ገልጸው ይህም የተፋሰስ ልማት ውጤት መሆኑን ገልጸዋል። የግራዋ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ አብዲሻ ጃፈር የዘንድሮው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ከሰባት ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የሚከናወን መሆኑን ገልፀዋል።   በተፋሰስ ልማቱ ላይ የተሳተፉ አርሶ አደሮች ባለፉት አመታት በሰሩት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ በርካታ ጥቅም እንዳስገኘላቸው ተናግረዋል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው የአካባቢውን ስነምህዳር በመጠበቅ ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል
Jan 13, 2026 281
አሶሳ፤ ጥር 5/2018 (ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሲከናወን የቆየው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአካባቢውን ስነምህዳር በመጠበቅ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የዘንድሮው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ደረጃ አሶሳ ዞን ቡልድግሉ ወረዳ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እና የአካባቢው ነዋሪዎች በተገኙበት ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ባበክር ሀሊፋ በወቅቱ እንደገለጹት፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአካባቢውን ስነምህዳር በመጠበቅ ምርታማነት እንዲጨምር አድርጓል። በተለይም የተፋሰስ ልማት ስራ በሚከናወንባቸው አካባቢዎች የሚተከሉ ችግኞች አፈርና ውሃን ከመጠበቅ ባለፈ ለአርሶአደሩ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ እያስገኙ ነው ብለዋል።   በዘንድሮው ዓመት ከ57 ሺህ ሄክታር በላይ ማሳ ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ለማከናወን እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ህብረተሰቡ ጥቅሙን በመረዳት በየአካባቢው ተሳትፎውን እያሳደገ መሆኑን ጠቅሰዋል። በክልሉ እየተከናወነ የሚገኘው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ በደለል እንዳይሞላ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውም ኃላፊው አንስተዋል።   የቡልድግሉ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ በክሪ አብዱላሂ በበኩላቸው፤ በወረዳው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መከናወን ከጀመረ ወዲህ የደን ሽፋን እያደገ እና የአካባቢው አየር ንብረት እየተስተካከለ መምጣቱን ተናግረዋል። ወረዳው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ አቅራቢያ በመገኘቱ የሚከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው የጎላ ጠቀሜታ እንዳለው አክለዋል። በመርሃግብሩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።  
የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የልማትና የዕድገት ግቦችን ለማሳካት እያገዘ ነው
Jan 13, 2026 257
በደሌ፤ ጥር 5/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል እየተከናወነ የሚገኘው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የልማትና የዕድገት ግቦችን ለማሳካት እያገዘ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በኦሮሚያ ክልል ለቀጣዮቹ ሁለት ወራት የሚከናወነው የዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ስራ በዛሬው ዕለት በክልል ደረጃ በቡኖ በደሌ ዞን ዳቦ ሐና ወረዳ ተጀምሯል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ፣ የዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ስራ ከ6 ሺህ 300 በላይ ተፋሰሶች ላይ ይከናወናል ብለዋል።   ባለፉት ዓመታት በክልሉ በተከናወነው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የክልሉ የደን ሽፋን መጨመሩንና በብዙ ተጎድተው የነበሩ አከባቢዎች በማገገማቸው ምርታማነትም በመጨመር ላይ እንደሚገኝ አንስተዋል። የተፋሰስ ልማት ስራው በተለይም በግብርናው ዘርፍ ተቀርጸው እየተተገበሩ የሚገኙ ኢንሼቲቮች ስኬት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። በአጠቃላይ በክልሉ እየተከናወነ የሚገኘው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የልማትና የዕድገት ግቦችን ለማሳካት ትልቅ አበርክቶ አለው ብለዋል። ዘንድሮም በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ በጠንካራ የህዝብ ተሳትፎ ታጅቦ የሚከናወን መሆኑን ገልጸዋል። የቡኖ በደሌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አማን ደኑ በበኩላቸው በዞኑ የተጀመረው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በ222 ተፋሰሶች ላይ የሚከናወን መሆኑን ገልጸዋል።   በዞኑ በአየር ንብረት ለውጥ እና በአፈር አሲዳማነት ምክንያት የሚደርሰውን የምርታማነት መቀነስን ለመከላከል በተፋሰስ ልማቱ የሚከናወኑ ስራዎች እንደሚጠናከሩ ተናግረዋል። በበጋው ወራት የተፋሰስ ልማት የሚከናወንበት መሬት በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተለያዩ ቸግኞች ለመሸፈን የቅድመ ዝግጅት ስራ እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል። ለዚህም ከ200 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በዞኑ እየተዘጋጁ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተፋሰስ ልማት ስራው የተሳተፉ አርሶ አደሮችም ስራው በአፈርና እና ውሃ ሀብቶች ላይ የሚደርሱ ችግሮችን በመከላከል ተጠቃሚነታቸውን የሚያረጋግጥ በመሆኑ ዘንድሮም ተሳትፏቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል።  
በመዲናዋ እየተከናወነ ያለው የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራ አካታች እና ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን የያዘ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jan 12, 2026 206
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ እየተከናወነ ያለው የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራ አካታች እና ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን የያዘ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። በአዲስ አበባ በሚገኙ ስምንት ወንዞች ላይ 47 ኪሎ ሜትር የሚረዝም የወንዝ ዳርች ልማት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። ከንቲባዋ ይህን ያሉት በከተማዋ እየተገነቡ ከሚገኙ ስምንት የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች መካከል የቀበና እና የግንፍሌ ወንዞችን የሥራ ሂደት በገመገሙበት ወቅት ነው።   ከንቲባ አዳነች አቤቤ ወንዞች ለከተማ መቆርቆር፣ ለከተማ ውበት እና ለከተማ ልማት ዋና እና መሰረት ናቸው ሲሉም ገልጸዋል። ይሁንና በአዲስ አበባ ወንዞች የብክለት ችግር የሚፈጠርባቸው፣ የተለያዩ ወንጀለኞች የሚደበቁበት፣ የበሽታ መንስኤዎች በመሆን ብዙ ተጽእኖዎችና ችግሮች ሲያደርሱ መቆየታቸውን አመልክተዋል። በኢትዮጵያ ወንዞች ላይ በተደረገ ጥናት በመዲናዋ ብቻ 76 ወንዞች እንዳሉ ጠቁመው ወንዞቹ ከየመጸዳጃ ቤቱ ፍሳሽ የሚገባባቸው ሆነው መገኘታቸውን ነው የገለጹት። በለውጡ ዘመን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ወንዞቻችንን እናጽዳ ሸገርን እናስውብ በሚል አዲስ አበባን እንደ ስሟ አበባ ከማድረግ ራዕይ ጋር በማስተሳሰር በ2012 ዓ.ም የወንዞች ዳርቻ ልማት መጀመሩን አስታውሰዋል።   ስራው አዲስ አበባ ውብ አበባ መሆን የምትችለው ወንዞች ከጸዱ እና ወደ ተፈጥሯዊ ማንነታቸው ከተመለሱ እና ከዳኑ ብቻ እንደሆነ በትልቅ መረዳት የተጀመረ እንደሆነም ነው ያስረዱት። የወንዝ ዳርቻ ልማት በወቅቱ ለኢትዮጵያ አዲስ በመሆኑ የውጭ የፋይናንስና የቴክኒክ ድጋፍ አስፈልጎ እንደነበር አመልክተዋል። ፕሮጀክቱ በተጀመረ አምስት ዓመታት ጊዜ ውስጥ ሁለት ኪሎ ሜትር የሚሆን ብቻ ልማት መከናወኑን ጠቅሰው በራሳችን ሀገር በቀል አቅም ለምን አንሰራም? በሚል የዛሬ ዓመት በአዲስ መልክ ስራው መጀመሩን ጠቁመዋል። በኢትዮጵያውያን አቅም በስምንት ወንዞች ላይ የ47 ኪሎ ሜትር የውንዝ ዳርቻ ልማት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም አብራርተዋል። ከዚህ ውስጥ ትልቁን ድርሻ የሚይዘው ከእንጠጦ እስከ ፒኮክ ያለው መሆኑን ገልጸው የውስጥ ለውስጥ መንገዶች እና መሰረተ ልማቶችን ሳይጨምር 21 ኪሎ ሜትር እንደሚረዝም ገልጸዋል። ከእንጠጦ እስከ ፒኮክ ባለው የወንዝ ዳርቻ ውስጥ ሰባት ፓርኮች እንደሚገኙና ንግድን ጨምሮ ሌሎች አገልግሎቶችን እንደሚሰጡም ተናግረዋል። በአጠቃላይ የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራው አካታች እና ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶችን የያዘ መሆኑን አክለዋል።
የውሃ ሃብት ሁሉንም የህይወት ዘርፍ የሚነካ ወሳኝ አህጉራዊ የህልውና ጉዳይ ነው
Jan 12, 2026 192
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ የውሃ ሃብት ለአፍሪካውያን ሁሉንም የህይወት ዘርፍ የሚነካ ወሳኝ አህጉራዊ የህልውና ጉዳይ መሆኑን የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። 39ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤና 48ኛው የሥራ አስፈፃሚዎች ምክር ቤት ስብሰባ ከየካቲት 4 እስከ 8 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ የአፍሪካ ሕብረት መሰብሰቢያ አዳራሽ ይካሄዳል። የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤን አጀንዳ፣ የውሳኔ ሀሳብና ሪፖርት ለማዘጋጀት የሚደረገው 51ኛው የሕብረቱ አባል ሀገራት ቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ ስብሰባ ዛሬ ተጀምሯል።   የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ ትኩረቱን በውሀ ላይ ያደረገ ነው። የውሃ ሃብት ለአፍሪካውያን ሁሉንም የህይወት ዘርፍ የሚነካ ወሳኝ አህጉራዊ የህልውና ጉዳይ ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፤ የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤና ኮፕ 30ን ለመከታተል ትክክለኛ ምርጫ ነው ብለዋል። የኮፕ 32 በአፍሪካ ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ በመመረጧ ኩራት ይሰማናል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረትና የተባበሩት መንግሥታት ለጉባኤው ዝግጅት በጋራ እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። 39ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ በሰላምና ጸጥታ ዙሪያ ብዙም ለውጥ ባልታየበት ሁኔታ እንደሚካሄድ ገልጸው፤ በሱዳን፣ ሊቢያ፣ በሳህል ቀጣና እና በምስራቃዊ ዲሞክራቲክ ኮንጎ ያለው ችግር እስካሁን አልተፈታም ብለዋል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን የሰላምና ደህንነት ምክር ቤት የአፍሪካ ችግሮች በአፍሪካውያን መፍትሔ እንዲያገኙ ለማስቻል በሰላምና ደህንነት የሪፎርም በጋራ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት ላይ የሚጣሉ የታሪፍ ገደቦች፣ የሚሰበሰበው ሀብት መቀነስና የጉዞ ክልከላዎች የዓለም ህግና ሥርዓቱን በመሸርሸር አሉታዊ ተፅዕኖ እያሳደሩ መሆኑንም አንስተዋል። በመሆኑም ይህንን ኢ-ፍትሐዊነት ለመከላከል በሕብረቱ አባል ሀገራት መካከል ትብብርና አንድነትን ማጠናከር ይገባል ብለዋል።   በአፍሪካ ሕብረት የአንጎላ ቋሚ ተወካይ እና 51ኛው የሕብረቱ አባል ሀገራት ቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ ስብሰባ ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ሚጉኤል ቤምቤ በአፍሪካ ዘላቂ የውሃ ሀብት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ መሪ ሀሳብ ውኃን መሰረት ያደረገ መሆኑን በማንሳት፤ በአፍሪካ በውኃ ጉዳዮች ላይ የሚነሱ ግጭቶችን መፍታት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ይመክራል ብለዋል፡፡ የዚህን መሪ ሀሳብ አመንጪ ኢትዮጵያ መሆኗን ያስታወሱት ፕሮፌሰር ሚጉኤል፤ ለአፍሪካውያን የቀረበ ሀሳብ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ በአፍሪካ ቀጣናዊ ትብብርና ኢኮኖሚያዊ ውህደት ለመፍጠር የኢንዱስትሪ አብዮት ወሳኝ መሆኑን በመግለጽ፤ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና በሁሉም አባል ሀገራት ገቢራዊ መደረግ አለበት ነው ያሉት፡፡ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና የአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 አካል ነው ያሉት ፕሮፌሰር ሚጉኤል፤ አህጉራዊ ግቦችን ለማሳካት ትብብርን ማጠናከር እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም