ቀጥታ፡
አካባቢ ጥበቃ
በምስራቅ ጎጃም ዞን በአረንጓዴ አሻራው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው አገር በቀል ችግኞች ተዘጋጅተዋል
Apr 20, 2026 88
ደብረ ማርቆስ፤ሚያዚያ 12/2018 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ጎጃም ዞን በአረንጓዴ አሻራ የሚተከሉ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው አገር በቀል ችግኞች በስፋት መዘጋጀታቸውን የምስራቅ ጎጃም ዞን የተፈጥሮ ሃብት መምሪያ አስታወቀ። በአረንጓዴ አሻራው የሚተከሉት ችግኞችም የተለያዩ ዝርያ ያላቸው መሆኑን በመምሪያው የተፈጥሮ ሃብት ቡድን መሪ አቶ ንጉሴ ሽመልስ ለኢዜአ ገልጸዋል። በዘንድሮው ዓመት በአረንጓዴ አሻራና በመደበኛው የክረምት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከ52 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን የተራቆተ መሬት ላይ ችግኞች እንደሚተከሉም ነው ያስረዱት። ከተዘጋጁት ችግኞች ውስጥም የኮሶ፣ የግራር፣ የወይራ፣ የጌሾ፣ የዋንዛ፣ የባህር ዛፍ፣ የሳስቫኒያ፣ የዲክረንስ፣ የፈረንጅ ጽድና ሌሎች የችግኝ ዓይነቶች እንደሚገኙበት ጠቁመዋል። ችግኞቹን ማዘጋጀት የተቻለውም ከ38 ሺህ በላይ በሚሆኑ የመንግስት፣ የማህበራትና የግል ችግኝ ጣቢያዎች መሆኑንም ነው ያስታወቁት። እንደ መምሪያው ገለጻ፥ በበጀት ዓመቱ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ከ261 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ ተከናውኗል።
በምስራቅ ቦረና እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም የችግኝ ተከላ እየተከናወነ ነው
Apr 20, 2026 90
ነገሌ ቦረና፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ፡- በምስራቅ ቦረና ዞን እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ እየተከናወነ መሆኑ ተገለፀ። በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ አልዬ አረባ ፤በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች ከ32 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለማፍላት ታቅዶ ሲሰራ ቆይቷል። እስካሁን በተካሄደው እንቅስቃሴ ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን በመቋቋም ኢኮኖሚያዊ ጥቅም የሚያስገኙ ከ25 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ለማዘጋጀት መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል የደን ዛፍ፣ የተለያዩ ፍራፍሬዎች እና የእንስሳት መኖ የሚሆኑት ዋነኞቹ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የተዘጋጁት ችግኞች በዞኑ ቆላማ ወረዳዎች ከመጋቢት አጋማሽ እስከ ሚያዝያ መጨረሻ ድረስ የሚጥለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም የሚተከሉ መሆኑን ተናግረዋል። እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀምም እስካሁን በ 2 ሺህ 83 ሄክታር መሬት ላይ ችግኞች መተከላቸውንም ነው ያስታወቁት። በችግኝ ተከላው በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ አደጋ የተራቆተ ከ7 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት በመከለል ለማልማት ትኩረት መሰጠቱን አመላክተዋል። በዘላቂ ልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እየተካሄደ ባለው የአረንጓዴ አሻራ እንቅስቃሴ ከ159 ሺህ በላይ ህዝብ እየተሳተፈ መሆኑንም ጠቁመዋል። በዞኑ እየተስፋፋ የመጣው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በየዓመቱ የሚከሰተውን ድርቅና የአካባቢ መራቆት ለመከላከልና ለመቋቋም ማስቻሉን አክለዋል። መርሃ ግብሩ ለዞኑ ህዝብ መሰረታዊ ችግር የነበረውን የመጠጥ ውሀና የእንስሳት መኖ እጥረት እያቃለለ መምጣቱንም ጠቅሰዋል። በዚህም በየዓመቱ ለዞኑ ህዝብ ከመንግሥት ሲቀርብ የነበረው የመጠጥ ውሀና የእንስሳት መኖ ድጋፍ ሙሉ ለሙሉ ለማስቀረት ማስቻሉን አብራርተዋል። በዝናብ አጠርና ቆላማ ወረዳዎች የተጀመሩት የበጋ መስኖ፣ የተፋስስ ልማትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተግባራት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ ሁለንተናዊ እገዛ ማድረጋቸውን አብራርተዋል።    
ኮፕ 32 ዘላቂ ትሩፋት ያለው ሆኖ እንዲያልፍ ለማድረግ ይሰራል - ዓለምጸሐይ ጳውሎስ
Apr 18, 2026 192
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ 32ኛው የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ32) ሂደት ዘላቂ የሆነ ትሩፋት ያለው ሆኖ እንዲያልፍ ለማድረግ እንደሚሰራ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሐይ ጳውሎስ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ32ኛው የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ32) ብሔራዊ ኮሚቴ የተከናወኑ ሥራዎችን ገምግመዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሐይ ጳውሎስ በዚሁ ወቅት የኮፕ32 መሠረተ ልማት፣ ሎጂስቲክስ እና ኦፕሬሽን ግብረ ኃይል የተከናወኑ ተግባራትን እና ትኩረት የሚፈልጉ ጉዳዮችን በሚመለከት ለኮፕ32 ‎ብሔራዊ ኮሚቴ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡   በማብራሪያቸውም የግብረ ኃይሉ ዓላማ ጉባዔው ከመካሄዱ በፊት አስፈላጊ የሆኑ ጉዳዮችን በማሟላት፤ ጉባዔው በሚካሄድበት ወቅት የተሳለጠ እንዲሆን እንዲሁም ከተጠናቀቀ በኋላ ትውልድ ተሻጋሪ የሆነ ዕሴት አሳርፎ ማለፍ እንዲችል ማድረግ ነው ብለዋል። በዚህም ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ እና መስፈርቶችን የሚያሟሉ መሠረተ ልማቶች የሚገነቡ እንዲሁም ከተለያዩ አካላት የሚሰባሰቡ አስፈላጊ ጉዳዮች መኖራቸውን ጠቁመዋል። ደኅንነቱ የተጠበቀ፣ የተሳለጠ እና ስኬታማ ጉባዔ ከማካሄድ በተጨማሪ ወደ ትውልድ መሻገር የሚችሉ፣ ዘላቂ እና ለቀጣይ ስራዎች አጋዥ የሚሆኑ መሠረተ ልማቶች መገንባትን ታሳቢ ያደረገ ዓላማን በመያዝ እየተሰራ ነው ብለዋል። ግብረ ኃይሉ መሠረታዊ የሚባሉ ግቦችን በመለየት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልጸው፤ የሚገነቡ መሠረተ ልማቶች ዓለም አቀፍ መስፈርቶችን የሚያሟሉ እና ጉባዔውን የሚያሳልጡ መሆናቸውን ማረጋገጥ የመጀመሪያው ግብ መሆኑን አመላክተዋል። የተገነቡ መሠረተ ልማቶች እንግዶች በጉባዔው ለመሳተፍ ሲመጡ ከአቀባበል ጀምሮ እስከሚሸኙበት ጊዜ ድረስ ደረጃውን የሚመጥን እንቅስቃሴዎች እንዲኖሩ በማድረግ ስኬታማ ጉባዔ እንዲካሄድ መሠረታዊ ጉዳዮችን የያዘ መሆኑን ተናግረዋል።   በዚህ ሂደት ነባሩ የከተማ እንቅስቃሴ እና የሕብረተሰብ አገልግሎት እንደተጠበቀ ሆኖ ነባሩን ሳይረብሽ አዲስ የሚመጣውን መቋቋም የሚችል የማይበገሩ መሠረተ ልማቶች መኖራቸውን የማረጋገጥ ግብ ሌላኛው ትኩረት የተደረገበት እንደሆነ መግለጻቸውን ኤፍ ኤም ሲ ዘግቧል። በሂደቱ የሚፈጠሩ አቅሞች በተለይም ወጣቶች በሂደት ውስጥ እንዲያልፉ በማድረግ የሀገር ውስጥ አቅምን መገንባት የሚያስችል ስራ እንደሚሰራም አብራርተዋል። በተጨማሪም ሙሉ ሂደቱ ዘላቂ የሆነ ትሩፋት ያለው ሆኖ እንዲያልፍ ማድረግን ታሳቢ በማድረግ እንደሚሰራ ገልጸው፤ ጉባዔው ከተለያዩ ጉዳዮች አኳያ ደኅንነቱ የተጠበቀ ሆኖ እንዲካሄድ የሚያስችል ግቦችን በመያዝ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በዞኑ የበጋ ወራት የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራዎች ምርታማነት እንዲጨምር አድርገዋል
Apr 18, 2026 110
አዳማ፤ ሚያዚያ 10/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የበጋ ወራት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጋቸውን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጽህፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንዳስታወቁት በዞኑ በየዓመቱ የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የአካባቢ መራቆትን ከማሻሻል ባለፈ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል።   ህብረተሰቡን በማሳተፍ የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎቹ የውሃ ምንጮች እንዲጎለብቱ በማድረግ ለመስኖ ልማት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አስረድተዋል። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራው የአፈር ለምነት እንዲጨምር እና በጎርፍ ይጠረግ የነበረን ለም አፈር በማስቀረት የግብርና ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጉን አስረድተዋል። የአፈርና ውሃ እቀባ ሥራዎች በተከናወነባቸው ተፋሰሶች ላይ በክረምቱ ወራት ችግኞችን በመትከልና በመንከባበከብ ህብረተሰቡ በእንስሳት ማድለብ፣ በንብ ማነብ፣ በፍራፍሬ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆን በቅንጅት መሰራቱንም አውስተዋል። በስራውም አርሶ አደሮች፣ ወጣቶችንና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች መሳተፋቸውን ጠቅሰዋል። የልማቱን ውጤታማነት ለማስቀጠልም በዘንድሮው የበጋ ወራት በ270 ተፋሰሶች ላይ የተለያዩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች በጠንካራ የህዝብ ተሳትፎ ማከናወን ተችሏል ብለዋል ከተከናወኑ ተግባራት በዋናነት 54 ሺህ 693 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የተለያዩ የእርከን ሥራዎች መሰራታቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል። ከዚህም በተጨማሪ ሰፋፊ የእርጥበት ማቆያ መዋቅሮችን ጨምሮ የተለያዩ ስነ-አካላዊ እና ስነ-ሕይወታዊ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን በስፋት መከናወናቸውን አቶ አብነት ጠቅሰዋል። የዞኑ አርሶ አደሮች የተፋሰስ ልማት ስራ ጠቀሜታውን በመረዳታችን በየዓመቱ ለአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራው ልዩ ትኩረት ሰጥተው መሳተፋቸውንም አንስተዋል። በአካባቢያቸው በተሠራው የተፈጥሮ ሀብት ሥራ ጎርፍን በመከላከልና የአፈር ለምነትን በመጠበቅ ለሰብል ምርታማነት ጉልህ አስተዋጾ እያደረገ መሆኑንም አመልክተዋል።      
በግብርናው ዘርፍ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ቀጥሏል
Apr 17, 2026 99
ደዋጨፋ፤ሚያዚያ 9/2018(ኢዜአ)፡-የክልሉን ሰላም በማጽናት በግብርናው ዘርፍ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለፁ። የፌዴራል፣ የአማራና የአፋር ክልሎች ከፍተኛ አመራሮች በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ዳዋጨፋ ወረዳ በኩታ ገጠም የለማ የፍራፍሬ ችግኝ ተከላን ዛሬ አስጀምረዋል።   የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ የክልሉን ሰላም በማጽናት የህብረተሰቡን ሁለተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ ነው። በተለይም በግብርውና ዘርፍ ዘመናዊ ቴክኖሎጂንና የተሻሻለ አሰራርን በመተግበር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት ሁሉን አቀፍ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   በክልሉ አካበቢን መሰረት ያደረገ የልማት አቅጣጫ እየተተገበረ መሆኑን ጠቁመው ዛሬ የተጀመረው ኩታገጠም የፍራፍሬ ልማትም ይህንኑ ከግምት ያስገባ ነው ብለዋል። የተጀመረውን የፍራፍሬ ልማት ወደ አፋር ክልል አጎራባች ወረዳዎች በማስፋት ጥራት ያለው የፍራፍሬ ምርትን ከአገር ውስጥ አልፎ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ያለመ መሆኑን ተናግረዋል።   የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሀጅ አወል አርባ በበኩላቸው የሁለቱን ክልል የህዝብ ለህዝብ ትስስር በልማትም አጠናክሮ ለማስቀጠል ቁርጠኛ አቋም ተወስዷል ብለዋል። በዚህም ዛሬ የተጀመረው የፍራፍሬ ልማት የሁለቱን ክልሎች አዋሳኝ ወረዳዎችን አካቶ በመተግበር የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል እንደሆነም ገልፀዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር)፣ በሀገሪቱ ሁሉም ክልሎች ያለውን ፀጋና ሀብት በጥናት ለይቶ በማልማት ለሀገር ብልፅግና ለማዋል ጥረት እየተደረገ ነው ብለዋል። በግብርናው ዘርፍ በጥራት፣ በአይነትና በብዛት በማምረት ከፍጆታ አልፎ ለወጭ ንግድ የሚተርፍ አመራረት ላይ በማተኮር ውጤት እየተገኘ መሆኑንም ተናግረዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች እየታየ ያለው ኩታ ገጠም የፍራፍሬ ልማት ለአገር እድገትና ለህዝብ ተጠቃሚነት ድርሻው የጎላ እየሆነ መምጣቱን አስረድተዋል።    
በደቡብ ኦሞ ዞን የበልግ ወቅት የችግኝ ተከላ ሥራ ተጀመረ
Apr 17, 2026 109
ዲመካ፣ ሚያዚያ 9/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኦሞ ዞን በተያዘው የበልግ ወቅት ከ4 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያላቸው ሀገር በቀል ችግኞች ተከላ ሥራ መጀመሩን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በዞኑ የ2018 ዓ.ም የበልግ ወቅት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ ተከላ ዛሬ በዲመካ ከተማ ተጀምሯል። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ በዚህ ወቅት እንደገለጹት በዞኑ በዘንድሮ የበልግ ወቅት ከ4 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያላቸው ሀገር በቀል ችግኞች ይተከላሉ።   ህዝቡን በማሳተፍ ለሚከናወነው የችግኝ ተከላ መርሀግብር ከ2 ሚሊዮን በላይ የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ተዘጋጅተው ዛሬ የመትከል ሥራው በይፋ መጀመሩን ተናግረዋል። የችግኝ ተከላ ሥራው ከአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ጎን ለጎን እንደሚካሄድ ገልጸው፣ ለግጦሽ ሣር የሚሆን ሥፍራን የመከለል ሥራም አብሮ ይከናወናል ብለዋል። እንደኃላፊው ገለጻ ዘንድሮ የሚተከሉት ችግኞች የአፈር መሸርሸርን ለመከላከል የሚያግዙ፣ ለምግብነት እና ለገቢ ምንጭነት የሚውሉ ፍራፍሬዎች እንዲሁም ለጥላነት የሚያገለግሉ ናቸው። በደቡብ ኦሞ ዞን ዲመካ ከተማ ዛሬ በተጀመረው የበልግ ወቅት የአረንጓዴ አሻራ መርሀሃ ግብር ችግኝ ተከላ ላይ የተሳተፉት አቶ ናደው ኤካደ በበኩላቸው በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ቀደም ሲል የተተከሉ ችግኞች ለተፈጥሮ አደጋ የነበራቸውን ተጋላጭነት እንደቀነሱላቸው ተናግረዋል። ልማቱ ያለውን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በአግባቡ በመረዳታቸው በተያዘው የበልግ ወቅትም ሆነ በመጪው የክረምት ወቅት በሚካሄድ የተከላ መርሀግብር የሚያደርጉትን ተሳትፎ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች እና የአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄዎች ተጨባጭ ውጤት እንዳመጡ የጠቀሱት ደግሞ አቶ ስጦታው አመዴ ናቸው። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች በተሰሩባቸው አካባቢዎች ተጨባጭ ለውጦች እንደመጡ ገልጸው፣ በተለይ ተራቁተው በነበሩ አካባቢዎች ችግኝ በመተከሉ እያገገሙ መሆናቸውን ተናግረዋል።  
ኢትዮጵያ ለኮፕ 32 ብሔራዊ ኮሚቴ አቋቁማ የዝግጅት ስራዎችን እያከናወነች ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 17, 2026 173
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለኮፕ 32 ብሔራዊ ኮሚቴ አቋቁማ የዝግጅት ስራዎችን እያከናወነች እንደምትገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት የኮፕ 32 አስተናጋጅ እንደሆነ ሀገር፤ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ኮሚቴ በይፋ በማቋቋም ዝግጅቷን ቀደም ብላ ጀምራለች ብለዋል።   ሂደቱን በግልጽ ግብ እና በላቀ ምልከታ ለመምራት ቁልፍ አመራር መመደቡና የኮፕ ፕሬዝደንት መዋቅርም የተቀናጀና የላቀ ውጤት የሚያስገኙ የቅድሚያ ተግባራቱን መጀመሩን ገልጸዋል። ዛሬ ከብሔራዊ ኮሚቴው ጋር በነበራቸው ስብሰባ በተለያዩ ዘርፎች የተከናወኑ ሥራዎችን በመገምገም ክፍተቶችን የመለየት እና ጥረቶች ከሀገራዊ ርዕይ ጋር የተጣጣሙ መሆናቸው መዳሰሱን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በመድረኩ የጋራ ቀጣይ አቅጣጫ መቀመጡን ጠቁመው፤ ትኩረቱም በጠንካራ ትብብር፣ በተዋሃደ ታላቅ ርዕይ እና በጋራ ጽኑ ትጋት ተናቦ ይህን ዓለም አቀፍ ሁነት በልህቀት በማስተናገድ የሀገርን ታላቅነት ዳግም ማሳየት መሆኑን አስታውቀዋል።
በክልሉ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በዝግጅት ላይ ከሚገኙ ችግኞች መካከል 70 በመቶው የፍራፍሬ ችግኞች ናቸው 
Apr 17, 2026 174
በጋምቤላ ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ልማት እየተዘጋጁ ከሚገኙት ችግኞች መካከል 70 ከመቶ የሚሆኑት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡ በክልሉ ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር በ70 የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ እንደሆነ ቢሮው ገልጿል። በቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ ኬት ቾል ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚያግዙና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ላላቸው ችግኞች ትኩረት ተሰጥቷል።   በዚህም 70 በሚሆኑ የግልና የመንግስት የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እየተዘጋጁ ከሚገኙት ችግኞች መካከል 70 ከመቶ የሚሆኑት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ተናግረዋል። ከችግኞቹ መካከል ማንጎ፣ አቮካዶ፣ ፓፓያ ፣ ዘይቱናና ሎሚ ዋነኞቹ እንደሆኑም ገልጸዋል። ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ልማት እየተዘጋጁ ካሉት የፍራፍሬ ችግኞች ባለፈ ከአካባቢው የአየር ንብረት ጋር የሚጣጣሙ የደን ችግኞች እየተዘጋጁ መሆናቸውንም ጠቁመዋል፡፡ በበጋው ወራት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የተከናወነባቸው ከዘጠኝ ሺህ ሄክታር በላይ የተራቆቱ አካባቢዎችን ስነ-ህይወት ለማልበስ የመረጣና የቦታ ልየታ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል።   በክልሉ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የተተከሉት የፍራፍሬና ሌሎች ችግኞች የአካባቢውን ስነ-ምህዳር ከመቀየር ባለፈ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በማገዝ ረገድ የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙም ተናግረዋል። በቀጣይም በክረምቱ ለሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ልማት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በሚያግዙ ችግኞች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
በክልሉ የህብረተሰቡ ችግኝ የመትከል ባህል እያደገ መጥቷል
Apr 16, 2026 146
ዋጂፎ፤ሚያዝያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የህብረተሰቡ ችግኝ የመትከል ባህል እያደገ መምጣቱን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) ገለጹ። በክልሉ ጋሞ ዞን የ2018 ዓ.ም የበልግ ወቅት የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር "አረንጓዴ አሻራ ለተምሳሌት ሀገር" በሚል መሪ ሃሳብ ዛሬ በምዕራብ አባያ ወረዳ ዋጂፎ ከተማ ተካሂዷል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በአየር ንብረት ለውጥ የሚከሰተውን የተፈጥሮ አደጋ በዘላቂነት ለመቋቋም ለችግኝ ተከላ ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል። የለውጡ መንግስት በአየር ንብረት ለውጥ የሚከሰትን ችግር መቋቋም እንዲቻል ለአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተተከሉ ችግኞች የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እያገዙ መሆኑን ጠቀመው፣ በክልሉ ህብረተሰቡ ችግኝ የመትከልና አካባቢውን የመንከባከብ ሥራ ባህሉ እያደረገ መምጣቱን ተናግረዋል።   የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አደጋ ለመከላከል ችግኝ ተከላን የዘወትር ተግባር ማድረግ እንደሚገባ ያሳሰቡት አበባየሁ (ዶ/ር)፣ ችግኝ ተከላው ለግብርና ምርታማነት፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ገቢን ለማሳደግ እያገዘ መሆኑን አስረድተዋል። ልማትን በዘላቂነት ለማረጋገጥ በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የሚከናወነውን የልማት ሥራ ማጠናከር ይገባል ያሉት ደግሞ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊና የዲላ ክላስተር አስተባባሪ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ናቸው።   መርሀ ግብሩ ለምግብ ዋስትና፣ ለዘላቂ ልማት፣ ለኢንዱስትሪ ሽግግር እንዲሁም ለምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥ የማይተካ ሚና ይጫወታል ብለዋል። በመሆኑም ዘንድሮ በክልሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እንደሚተከሉ የጠቀሱት መሪሁን (ዶ/ር)፣ ግብርናን በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነትን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማረጋገጥ እንደሚሰራም ተናግረዋል። የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ደምስ አድማሱ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት፣ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ በዜጎች ሕይወት ላይ ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ተናግረዋል።   በዘንድሮ የበልግ ወቅት በሚከናወን የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ከዘጠኝ ሚሊዮን በላይ የፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት በማድረግ ወደ ትግበራ መገባቱን አንስተዋል። በተለይ በዞኑ በተደጋጋሚ የሚከሰቱ የጎርፍ እና የመሬት መንሸራተት አደጋዎች ተፈጥሮን በአግባቡ ባለመንከባከብ የሚከሰቱ መሆናቸውን ጠቁመው፣ ለችግኝ ተከላው ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል።   በምዕራብ አባያ ወረዳ የዋጂፎ ከተማ ነዋሪ የሆኑት ሃምሳ አለቃ ዋጋሶ ኦቼ እና አቶ ዳንኤል ዳንጋሮ በበኩላቸው ቀደም ሲል በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የተተከሉ ችግኞች በአካባቢያቸው ተጨባጭ ውጤት ማምጣታቸውን ተናግረዋል። በየዓመቱ በተተከሉ ችግኞች ቀደም ሲል ሞቃት የነበረው የአካባቢው የዓየር ጸባይ እየተስተካከለ መምጣቱን የገለጹት ነዋሪዎቹ፣ በግብርና ሥራም ተጨባጭ ውጤት እየታየ መሆኑን ተናግረዋል። ለዚህም በመርሀ ግብሩ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውን ፍራፍሬዎች በማልማት ተጨማሪ ገቢ ከማግኘት ባለፈ፣ ለጓሮ አትክልትና ለእንስሳት መኖ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ይህን ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በዛሬው የችግኝ ተከላ መርሀግብር መሳተፋቸውን ገልጸው፣ በቀጣይም በችግኝ ተከላና እንክብካቤ የሚያደርጉትን አስተዋጽኦ እንደሚያጠናክሩ አረጋግጠዋል። በችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ እንዲሁም የከተማ አስተዳደር የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
በሶማሌ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የችግኝ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Apr 16, 2026 136
ጅግጅጋ፣ ሚያዝያ 8/2018(ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የችግኝ ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡ በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የተተከሉ ችግኞች የአካባቢን ስነምህዳር ከመቀየር ባለፈ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ በመስጠት ላይ መሆናቸው ይታወቃል። በሶማሌ ክልል አከባቢ ጥበቃና ገጠር መሬት አስተዳደር ቢሮ የደን ልማት ዳይሬክተር ሂቦ ኑር ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በለውጡ ዓመታት በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር በተከናወኑት የችግኝ ተከላ ተግባራት መሬት መራቆትና የአፈር መሸርሸርን መከላከል እየተቻለ ነው። በክልሉ በመርሃ ግብሩ የተተከሉት ችግኞች የአፈር መሸርሸርና የመሬት መራቆት በመከላከልና የአየር ንብረት ተጽዕኖ ለመቋቋም አበረታች ለውጥ ያመጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዘንድሮው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም በክልሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለመትከል ታቅዶ የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የታቀደውን የችግኝ ተከላ መርሃግብር ለማሳካት በ160 የግልና የመንግስት ችግኝ ጣቢያዎች ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆናቸውንም ተናግረዋል። ችግኞቹ ለማህበረሰቡ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን የሚሰጡ፣ ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ዓይነቶች፣ ለደንነት የሚውሉ፣ ለውበትና ለእንስሳት መኖ የሚሆኑ መሆናቸውን ተናግረዋል። ህብረተሰቡም የሚተከሉ ችግኞችን በመከታተልና አስፈላጊውን እንክብካቤ በማድረግ የደን ሽፋን ለመጨመር የበኩሉን እንዲወጣ ዳይሬክተሩ አስገንዝበዋል።
በክልሉ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አመርቂ ውጤት ተገኝቶበታል 
Apr 15, 2026 110
ወላይታ ሶዶ ፤ ሚያዚያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞች አመርቂ ውጤት የተገኘባቸው መሆኑን የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ ተናገሩ። በክልሉ የ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ የበልግ ወቅት ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር "አረንጓዴ አሻራ ለተምሳሌት ሀገር ብልፅግና" በሚል መሪ ሃሳብ በወላይታ ዞን ሶዶ ዙሪያ ወረዳ ሼላ ቦርኮሼ ቀበሌ ተካሂዷል።   የክልሉ መንግስት ዋና ተጠሪ አቶ ገብረመስቀል ጫላ በወቅቱ እንደገለጹት፤ ባለፉት የለውጥ አመታት ተግባራዊ የተደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አመርቂ ዉጤት ተገኝቶበታል፡፡ መርሃ ግብሩ የተራቆቱና ከጥቅም ውጭ የነበሩ መሬቶች ለምተው እንደገና ጥቅም እንዲሰጡ ከማድረጉ ባሻገር 18 ነጥብ 95 ከመቶ የነበረውን የክልሉን የደን ሽፋን ወደ 23 ነጥብ 86 ከመቶ በላይ ለማሳደግ ማስቻሉን ገልጸዋል። የችግኝ ተከላው ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ በመሆኑም ለተያዘው የበልግ ወቅት የችግኝ ተከላም በቂ ዝግጅት መደረጉን አመልክተዋል። በዘርፉ የመጣውን ለውጥ ለማስቀጠልም ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በነቂስ ወጥቶ ችግኝ መትከልና መንከባከብ እንደሚገባውም አሳስበዋል። በምክትል ርዕሰ-መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊና የዲላ ክላስተር አስባባሪ መሪሁን ፍቅሩ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸዉ ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ እየተሰራ ነዉ ብለዋል፡፡   በበጋው ወራትም 1 ሺህ 384 የማህበረሰብ ተፋሰስ ውስጥ 159 ሺህ ሄክታር መሬት በዋና ዋና የአፈርና ዉሃ ጥበቃ ስራዎች መሸፈናቸውም ገልጸዋል። በበልግ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የጥምር ደን ፣ የፍራፍሬ ፣ የሀገር በቀል እጽዋት፣ የቡና ፣ የእንሰት ፣የጥላና የጌጥ ዛፍ ችግኞች ተከላ እንደሚደረግም ጠቁመዋል። ባለፉት ሰባት ዓመታት በተካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተጎድቶ የነበረውን የተፈጥሮ ሀብት መመለስ ተችሏል ያሉት ደግሞ የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ ናቸው፡፡   በአሁኑ ወቅትም በዞኑ 16 ተራራዎችን ለማልማት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዘንድሮ የበልግ ወቅት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብርም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ እየተሰራ እንደሆንም አብራርተዋል።
በሐረሪ ክልል ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተጠናከረ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Apr 15, 2026 117
ሐረር ፤ ሚያዚያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ በሐረሪ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ልማት መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ዝግጅቶች እየተካሄዱ መሆኑን የክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡ በክልሉ ግብርና ቢሮ የተፈጥሮ ሀብት ልማት አጠቃቀም እና ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ አራርሶ አደም፤ ለኢዜአ እንደገለጹት ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ላላቸው የችግኝ ዓይነቶች ትኩረት ተሰጥቷል። የአረንጓዴ አሻራ ልማት ስራዎችን ስኬታማ ለማድረግ ከወዲሁ የችግኝ ማፍላትና የተከላ ቦታ መለየትን ጨምሮ ልዩ ልዩ ዝግጅቶች እየተካሄዱ ነው ብለዋል። በመጪው ክረምት በክልሉ የተራቆቱ አካባቢዎችን ስነ-ምህዳር ለመመለስ የሚያስችሉና የደንነት ጠቀሜታ ካላቸው ችግኞች በተጓዳኝ ሌሎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እየፈሉ መሆኑን ተናግረዋል።   ችግኞቹም በመንግስት የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎችና በግለሰቦች እየተዘጋጁ መሆኑን አንስተው ከእነዚህ ችግኞች መካከል 70 በመቶ የሚሆኑት የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን አብራርተዋል። ቀሪዎቹ ችግኞች ደግሞ ሀገር በቀል ዛፎችና፣ ለእንስሳት መኖና ለደን አገልግሎት የሚውሉ መሆናቸውን አቶ አራርሶ አክለዋል። ጥምር ጥቅም የሚሰጡት የአፕል፣ የማንጎና የአቮካዶ ችግኞችም በክላስተር እንደሚተከሉ ጠቁመዋል። በክረምቱ ወራት በክልሉ የሚተከሉት ችግኞች 1ሺህ ሄክታር የሚሆን መሬት በስነ ህይወት ለማልበስና መልሶ ለማልማት ግብ መቀመጡን ጠቁመው ለዚህም ከወዲሁ የቦታ መረጣ ስራ መከናወኑን ገልጸዋል። ችግኞቹ በተራቆቱ አካባቢዎችንና በማህበረሰቡ ተሳትፎ በ600 ሄክታር መሬት የተፋሰስ ልማት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ቦታ ላይ እንደሚተከሉም አስረድተዋል፡፡ ባለፈው ክረምት በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ ልማት መርሃ ግብር በተራቆቱ አካባቢዎች የተተከሉት ችግኞች በሚደረግላቸው እንክብካቤ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙም አቶ አራርሶ አክለዋል።
በድሬዳዋ አስተዳደር ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል 
Apr 15, 2026 198
ድሬዳዋ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፡- በድሬዳዋ አስተዳደር ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የፍራፍሬ እና ለደንነት የሚውሉ ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን የአስተዳደሩ የአካባቢ፣ ደንና አየር ንብረት ባለስልጣን አስታወቀ። ባለፉት የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ዓመታት በአስተዳደሩ የተተከሉ ችግኞች የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የገጠሩን ማህበረሰብ ከተረጂነት ወደ አምራችነት እያሸጋገሩ መሆናቸውም ተመላክቷል። በድሬደዋ አስተዳደር የአካባቢ፣ ደንና አየር ንብረት ባለስልጣን የደን ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ ማስረሻ ይመር ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር በአስተዳደሩ በሚገኙ ከ20 በላይ የችግኝ ጣቢያዎች የተለያዩ ችግኞች በጥራት እየተዘጋጁ ነው። ከአስተዳደሩ ግብርና፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ጋር በመቀናጀት የተለያዩ የፍራፍሬ፣ የደንና የውበት ችግኞች በማፍላት ለተከላ ዝግጁ እየተደረጉ ይገኛሉ ብለዋል። በዘንድሮ ክረምት ከሚተከሉት ችግኞች መካከል 60 በመቶ የሚሆኑት ከድሬደዋ ስነምህዳርና አየር ንብረት ጋር ስምሙ የሆኑ የተለያዩ ፍራፍሬዎች መሆናቸውን አንስተዋል።   የሚተከሉት ፍራፍሬዎች በተለይም የገጠሩን ማህበረሰብ ከተረጂነት ወደ አምራችነት ለማሸጋገርና የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥ እያገዙ መሆናቸውን በማስገንዘብ። አቶ ማስረሻ አክለውም ባለፉት የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር በአስተዳደሩ የተተከሉት ችግኞች ከ80 በመቶ በላይ ፀድቀው የግብርናን ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ምቹ መደላድል ከመፍጠር በዘለለ የሌማት ትሩፋት መርሃግብርን ውጤታማ እያደረጉ መሆኑን አስታውቀዋል። በባለስልጣኑ የደን ልማት ቡድን መሪ አቶ ማሙሽ ዘውዴ በበኩላቸው፤ ባለፉት ሰባት የአረንጓዴ አሻራ ዘመቻ የተተከሉት ችግኞች የድሬዳዋን በረሃማ ስነምህዳር በመቀየር የከተማዋን የጎርፍ ተጋላጭነት እያስቀሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በተለይም በገጠር ቀበሌዎች የተተከሉት የሎሚ፣ የፓፓያ፣ የብርትኳን እና ሌሎች ምርጥ የፍራፍሬ ችግኞች የአርሶአደሩን ገቢ በመጨመር እና ለወጣቶች የስራ ዕድል በመፍጠር ተጨባጭ ውጤቶች እያስገኙ ናቸው ብለዋል። እነዚህን ፍሬያማ ውጤቶች ለማስቀጠል በአሁን ሰዓት እየጣለ የሚገኘውን የበልግ ዝናብ ጥቅም ላይ በማዋል 75 ሺህ የፍራፍሬ ችግኞች በገጠር ቀበሌዎች መተከላቸውን ለአብነት አንስተዋል።   እንደ አቶ ማሙሽ ገለፃ ባለፈው ጥር ወር የተካሄደው የተፋሰስ ልማት በአስተዳደሩ ለሚተከሉት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች የጉድጓድ ቁፋሮ እና ሌሎች ዝግጅቶች በከፊል እንዲጠናቀቁ አስችሏል። እነዚህ የቅድመ ተከላ ዝግጅቶች የመጪውን ክረምት የችግኝ ተከላ በላቀ እና በተናበበ መንገድ ዳር ለማድረስ እንደሚያስችሉም አንስተዋል። በአስተዳደሩ ባለፉት ሰባት የአረንጓዴ አሻራ ዘመቻዎች ህብረተሰቡንና ባለድርሻዎችን በማስተባበር የተለያዩ የደን፣ የውበት እና የፍራፍሬ ችግኞች ተተክለው የድሬደዋን የደንና ስነምህዳር በከፍተኛ ደረጃ እየለወጡ መሆናቸውን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።
በመጪዎቹ ሁለት ሳምንታት የበልግ ተጠቃሚ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ ዝናብ ያገኛሉ
Apr 14, 2026 117
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡-በመጪዎቹ ሁለት ሳምንታት የበልግ ተጠቃሚ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ ዝናብ እንደሚያገኙ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ በመጪዎቹ ሁለት ሳምንታት ለበልግ ዝናብ መፈጠር ምቹ ሁኔታን የሚፈጥሩ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች ይበልጥ እንደሚጠናከር አስታውቋል። በዚህም በልግ ዋነኛና ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸዉ በሆኑት የደቡብ ኢትዮጵያ፣ ደቡብ ኦሮሚያ ዞኖች፣ ስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎች፣ መካከለኛው፣ ሰሜን ምስራቅ አካባቢዎች የተሻለ የዝናብ ስርጭት እንደሚኖራቸው ተገልጿል። የደቡብ ምዕራብ፣ ሰሜን ምዕራብ እና ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎችም እንዲሁ። የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎችን ጨምሮ ሰሜን ምዕራብና የምዕራብ የሀገሪቱ ቦታዎቻቸውን የሚሸፍን ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ ተብሏል። በተጨማሪም በደቡብ ምዕራብ፣ ሰሜን ምስራቅ እና ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች በ24 ሰዓት ውስጥ ከ30 ሚ.ሜ በላይ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ተገልጿል። በሚያዚያ የመጀመሪያዉ አስር ቀናት ከሚኖረው ከፍተኛ የፀሐይ ሀይል ጋር በተያያዘ በተለይም በጋምቤላ፣ በአፋር፣ በሶማሌ፣ በቤንሻንጉል-ጉሙዝና በምዕራብ አማራ አካባቢዎች ላይ የቀኑ ከፍተኛ ሙቀት ከ3 እስከ 41 ዲግሪ ሴልሺየስ እንደሚሆንም ተመላክቷል። በመደበኛ ሁኔታ የበልግ ዝናብ በአብዛኛዎቹ በልግ ዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎች ላይ እስከ ሚያዚያ የመጨረሻዎቹ አሥር ቀናት ቀጣይነት የሚኖረው ሲሆን በተጨማሪም ከሚጠናከሩት ሚቲዎሮሎጂ ክስተቶች ጋር ተያይዞ ወቅታዊው ዝናብ ቀስ በቀስ ወደ ምዕራብ አጋማሽ የሀገሪቱ ክፍሎች ላይ እንደሚስፋፋ ተገልጿል። በሚያዚያ የመጪዎቹ አሥር ቀናት በአብዛኛዎቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ ዝናብ ቀጣይነት እንደሚኖረው የትንበያ መረጃዎች ጠቁመዋል። ከዚሁ ጋር በተያያዘም በደቡብ፣ ደቡብ ምዕራብ፣ ምዕራብ፣ ምስራቅ እንዲሁም በስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች የተሻለ የዝናብ ገጽታ እንደሚኖራቸው ትንበያው አመላክቷል። በመሆኑም በልግ አብቃይ አካባቢዎች በርካታ ቦታዎቻቸውን የሚሸፍን ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ ተብሏል። በደቡብ እና በደቡብ ምዕራብ የሀገራችን አካባቢዎች ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ተመላክቷል። ዋነኛ እና ሁለተኛ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚና የበልግ ሰብል አብቃይ በሆኑት የደቡብ ኢትዮጵያ፤ የደቡብ ኦሮሚያ ዞኖች የስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎችና የመካከለኛው የሰሜን ምስራቅ አካባቢዎች የተስፋፋ እርጥበት እንደሚያገኙ ተመላክቷል። እንዲሁም የደቡብ ምዕራብ ሰሜን ምዕራብ እና ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተስፋፋ እርጥበት ያገኛሉ ተብሏል። በመሆኑም አርሶ አደሮች አርብቶ አደሮች እና የሚመለከታቸው አካላት የሚጠበቁ መልካም ሁኔታዎችን በአግባቡ ሊጠቀሙ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አሳስቧል። እንዲሁም ሊኖር የሚችሉ ተያያዥ ስጋቶችን ለመቀነስ የተቀመጡትን ቦታ ተኮር የግብርና ሚቲዎሮሎጂ ምክረ ሀሳቦች ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባም ኢንስቲትዩት አስገንዝቧል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር ለግብርና ምርትና ምርታማነት ገንቢ ሚና እየተወጣ ነው
Apr 14, 2026 250
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምግብ ስርዓትን በማሻሻል፤ ገበያን በማሳደግና ሥነ ምህዳርን በመመለስ ለግብርና ምርትና ምርታማነት ገንቢ ሚና እየተወጣ መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር ኢያሱ ኤልያስ ገለጹ። የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት /አግራ/ የተመሰረተበትን 20ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የከፍተኛ ባለሙያዎችና የሥራ ሀላፊዎች ውይይት ተካሄዷል።   የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር ኢያሱ ኤልያስ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በአፍሪካ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ዘላቂ ዕድገት ለማስመዝገብ የግብርና ሽግግር ወሳኝ ነው። የግብርና ሽግግርን ለማረጋገጥ ደግሞ ለአርሶ አደሩ ዘላቂ የኢንቨስትመንት ዕድሎችን መፍጠር ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ የግብርና ሜካናይዜሽንን በማሳደግ፣ ጠንካራ የፖሊሲ ርምጃ በመከተልና ቁርጠኛ አመራር ውሳኔ በመስጠት በግብርናው ዘርፍ እመርታዊ ለውጥ ማስመዝገቧን ገልጸዋል። በዚህም ኢትዮጵያ የአፍሪካ ቀዳሚ የስንዴ አምራችና ከፍተኛ የቡና ምርት ላኪ መሆን መቻሏን ገልጸው፤ የመስኖ ልማትና የኤክስቴንሽን ስራዎች ውጤት አበርክቶ የላቀ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ ግብርና የአግሮ ፎረስትሪ ስትራቴጂ እና ሌሎች ኢንሼቲቮችን በመጀመር የምርት ስርዓቱ እንዲቀየር፣ የትራክተርና ኮምባይነር ግብዓት በዕጅጉ እንዲሻሻል መደረጉን ገልጸዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካባቢን በመጠበቅ፣ ገበያን በማሳደግና የምግብ ስርዓትን በማሻሻል ለግብርና ምርትና ምርታማነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል ብለዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገርና በቴክኖሎጂ የታጠቀ የግብርና ሥርዓት እየተገበረች መሆኑንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ሁሉን አቀፍ ሽግግር በመፍጠር የገጠር ሽግግር፣ ዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትና የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ግብ ይዛ እየሰራች መሆኑን ተናግረዋል። አግራ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም በሚያስችሉ ስራዎች ላይ በማማከር፣ በመስኖ ልማትና የተሻሻለ ግብርና ላይ በማተኮር ለአነስተኛ አርሶ አደሮች ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት /አግራ/ ፕሬዝዳንት አሊዝ ሩዌዛ በበኩላቸው፤ በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጫና እና የዜጎች የምግብ ፍላጎት መጨመር ትርጉም ያለው የኢኮኖሚ እድል መፍጠርን ይጠይቃል ብለዋል፡፡   በተለይም የወጣቶችን ተጠቃሚነት ማሳደግ ፈጣን ምላሽ የሚያስፈልገው መሆኑን ጠቅሰው፤ በትብብርና በትኩረት መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ በጠንካራ አመራርና ውሳኔ ሰጭነት በግብርናው ዘርፍ ስኬት አስመዝግባለች ያሉት ፕሬዝዳንቷ፤ በምርምር፣ ሳይንስና ቴክኖሎጂ የተደገፉ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ብለዋል፡፡ የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት /አግራ/ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ይሄነው ዘውዴ (ዶ/ር)፤ ባለፉት 20 ዓመታት ከኢትዮጵያ ጋር በጠንካራ ትብብር መስራታቸውን ገልጸዋል።   አግራ ጥምረት በመሆኑ በትብብር ያምናል ያሉት ዳይሬክተሩ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር ባለሙያዎችን በማሰማራት ሲሰራ መቆየቱንም ተናግረዋል።
በክልሉ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስነ-ምህዳርን መሰረት ያደረገ የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ ነው
Apr 14, 2026 171
‎ባህርዳር፤ ሚያዚያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በመጪው ክረምት ለሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውና የአካባቢ ስነ-ምህዳርን መሰረት ያደረጉ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ‎የቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንደገለፁት፤በመጭው የክረምት ወቅት የሚተከሉ አንድ ነጥብ ሰባት ቢሊዮን ችግኞችን ለማዘጋጀት ታቅዶ እየተሰራ ነው።   እስካሁን በተደረገው ጥረትም ከአንድ ቢሊዮን በላይ ችግኞችን ማፍላት የተቻለ ሲሆን ቀሪውን ባጭር ጊዜ በማዘጋጀት ለተከላ ዝግጁ እንደሚደረግም ተናግረዋል። ዝግጁ በመደረግ ላይ ያሉት ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ኮሶ፣ ወይራ፣ ባህር ዛፍ ፣ የአበሻና የፈረንጅ ፅድ፣ አካሺያ ዲከረንስና ሌሎች ሀገር በቀልና የውጭ ዝርያ ያላቸው ችግኞች ናቸው ብለዋል። ሊዚሁ የችግኝ ተከላ መርሃግብርም ከ200 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የመለየት ስራ መሰራቱንም አስገንዝበዋል። በክልሉ ‎ባለፈው የክረምት ወቅት ከተተከለው ከአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን በላይ ችግኝ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው መጽደቁን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመለክታል። ‎ ‎  
በኦሮሚያ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር በርካታ ጥቅም ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Apr 14, 2026 121
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ከ1 ሚሊዮን ሔክታር በሚልቅ አዲስ መሬት ላይ የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የልማትና ደን እንክብካቤ ዳይሬክተርና የዘርፉ ተወካይ ከተማ አብዲሳ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር በተተከሉ ችግኞች ውጤት ተገኝቷል። በዚህም መሠረት ዘንድሮ በችግኝ ለመሸፈን ከታቀደው መሬት በ50 በመቶው በላይ ለምግብነት የሚውሉ ችግኞች እንደሚተከሉ ገልጸው፤ አጠቃላይ የዝግጅት ተግባራቱም 92 በመቶ መድረሱን አስታውቀዋል። በክልሉ ዘንድሮ ለአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ከ1 ሚሊየን ሔክታር በላይ አዲስ መሬት መዘጋጀቱንም አረጋግጠዋል። ከዚህ ውስጥም ለደን የሚያገለግሉ ችግኞች ከ400 ሺህ ሔክታር በሚልቅ መሬት ላይ በኩታ ገጠም እንደሚተከሉ አስረድተዋል። የሚተከሉ ችግኞች የመሬት ለምነትን የሚመልሱ፣ ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ፣ ከሚለማው ሰብል ጋር የሚስማሙና አርሶ አደሩ በውስን መሬት ላይ ሁለገብ ተጠቃሚ እንዲሆን የሚያስችሉ ናቸው ብለዋል። በመንግሥት፣ በኢንተርፕራይዞች፣ በማኅበራትና በአርሶ አደሮች አማካኝነት፤ በ1 ሺህ 200 የችግኝ ጣቢያዎች ችግኝ እየተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል። አሁን ላይ የዝናብ እጥረት ያለባቸው አካባቢዎች እርጥበትን በመቆጠብ ውኃን ይዘው ማቆየት የሚችሉ የችግኝ ጉድጓዶች እየተዘጋጁ መሆኑንም አመላክተዋል።  
በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ከ142 ሚሊዮን በላይ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Apr 13, 2026 176
ጎንደር፤ ሚያዚያ 5/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ከ142 ሚሊዮን በላይ ሀገር በቀል ችግኞች የማዘጋጀት ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ የመምሪያው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን አጠናክሮ በማስቀጠል የአካባቢውን ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው።   ለዚህም በዞኑ ሥር ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች በተቋቋሙ 12ሺህ የችግኝ ጣቢያዎች ከ142 ሚሊዮን በላይ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውና የአካባቢውን ስነ ምህዳር ለመጠበቅ የሚያግዙ ችግኞች እየፈሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ችግኞቹ በመጪው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የሚተከሉ መሆናቸውን ገልጸው፣ እስካሁን በተደረገ ጥረትም ቀድመው የሚፈሉ 76 ሚሊዮን ሀገር በቀል ችግኞችን በማፍላት የእንክብካቤ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡   በክረምቱ ከሚተከሉ ችግኞች ውስጥ ከ40 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ኢኮኖሚያዊ ጥቅም የሚሰጡ አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ቡናና መሰል የፍራፍሬ ችግኞች እንደሆኑም አስረድተዋል። እንደ አቶ ንጉሴ ገለጻ፣ በመጪው ክረምት 33ሺህ ሄክታር የሚሸፍን የችግኝ ተከላ ሥራ ለማከናወን የቦታ መረጣና ሌሎች ዝግጅቶች እየተደረጉ ይገኛሉ።፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአካባቢን ስነ ምህዳር ከማስጠበቅ ባለፈ በርካታ ወጣቶች በግላቸው ችግኝ አፍልተው በመሸጥ የሥራ ዕድል እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም አያይዘው ገልጸዋል።   የዞኑ ህብረተሰብ ችግኝ የተተከለባቸውን ቦታዎች ከመከለል ባለፈ በራሱ ወጪ ሠራተኞችን ቀጥሮ የእንክብካቤና የጥበቃ ሥራ እያከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ ባለፈው ዓመት ክረምት ከተተከሉ 121 ሚሊዮን በላይ ችግኞች 86 በመቶው ጸድቀዋል ብለዋል። የደን ልማት ሥራ ለግብርና ሥራችን መሰረት በመሆኑ በየዓመቱ በክረምት ወራት ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ ተሳትፎ እያደረጉ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የወገራ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር በላይነህ ስጦታው ናቸው፡፡ የጎንደር ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ ወጣት አምሳሉ ገነቱ በበኩሉ እንዳለው እሱና ጓደኞቹ በማህበር ተደራጅተው ባቋቋሙት የችግኝ ጣቢያ ሀገር በቀል የዛፍና የፍራፍሬ ችግኞችን አፍልተው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እየሆኑ መጥተዋል፡፡   ለመጪው ክረምትም ከ500 ሺህ በላይ ችግኞች በማፍላት ለገበያ ለማቅረብ እየተዘጋጁ መሆኑን ጠቁመው፣ ከችግኞቹ መካከል ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የአቮካዶ እና የማንጎ ዝርያዎች ይገኙበታል ብለዋል። የማዕከላዊ ጎንደር ዞን አሁናዊ የደን ሽፋን መጠን 15 ነጥብ 2 በመቶ መድረሱን ከዞኑ ግብርና መምሪያ የተገኘ መረጃ ያመለክታል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የፖለቲካ ቁርጠኝነትና የሕብረተሰብ ንቁ ተሳትፎ የታየበት በአፍሪካ ቀዳሚ ኢንሼቲቭ ነው
Apr 9, 2026 136
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡-የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የፖለቲካ ቁርጠኝነትና የህብረተሰብ ንቁ ተሳትፎ የታየበት በአፍሪካ ቀዳሚ ኢንሼቲቭ መሆኑን የብሄራዊ አረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ ሰብሳቢ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያ የምታስተናግደው 16ኛው የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አህጉራዊ ጉባኤ "ለሉዓላዊነት መተባበር" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን እየተካሄደ ነው።   የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አባል ሀገራትና ታዛቢዎች እንዲሁም የዘርፉ ተዋንያን የሚሳተፉበት ጉባኤው በአፍሪካውያን መካከል ትብብርና አጋርነትን በመፍጠር አህጉራዊ የአደጋ ሥጋትን የመከላከልና የፋይናንስ አቅምን ማጠናከርን ያለመ ነው። ጉባኤው የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም፣ ለአደጋ ስጋት ምላሽ ለመስጠት እና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ አፍሪካ መር መፍትሔ ማፈላለግ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ምክክርና የጋራ መግባባት መፍጠር ያስችላል። የብሄራዊ አረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ ሰብሳቢ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) በመድረኩ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያስመዘገበችውን ስኬትና ለአፍሪካ ያላትን ተሞክሮ አቅርበዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የመጀመሪያ ምዕራፍ 50 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ስታቅድ በወቅቱ ምሁራን ሳይቀሩ ዕቅዱ ሊሳካ አይችልም የሚል ጥርጣሬ እንደነበራቸው አስታውሰዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እሳቤ መሆኑን ጠቅሰው፤ የተራቆተ መሬትን እንዲያገግም ማድረግ ሥነ-ምህዳሩን መመለስ እና ለግብርናና ከተማ ልማት ምቹ ከባቢ መፍጠር ነው ብለዋል። በዚህም የተለያዩ ሀገር በቀል እና ለተለያዩ አገልግሎት የሚውሉ ችግኞችን በመትከል የኢትዮጵያን ምድር አረንጓዴ ማልበስ መጀመሩን ገልጸዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከቀጣይነት ያለው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃን በማጠናከር የግብርና ሥራዎች ምቹ ሥነ-ምህዳር መፍጠሩን ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ የመላው ኢትዮጵያውያንና ተቋማት ትብብር የጋራ ውጤት ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ ከጠቅላይ ማኒስትሩ ጀምሮ የሁሉም አመራር ቁርጠኝነት የታየበት መሆኑን ጠቅሰው፤ ለጎረቤት ሀገራት ጭምር ተሞክሮ ሆኗል ብለዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጭምር ተቀባይነት ማግኘቱን ገልፀው፣ ኬንያ በአስር ዓመት ውስጥ 15 ቢሊየን ችግኝ ለመትከል ተሞክሮ መውሰዷን ተናግረዋል።  
ለአየር ንብረት ለውጥ የማትበገር አፍሪካን ለመገንባት አህጉራዊ አንድነታችን ወሳኝ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 9, 2026 243
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡- ለአየር ንብረት ለውጥ የማትበገር አፍሪካን ለመገንባት አህጉራዊ አንድነታችን ወሳኝ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ዛሬ በሰው ልጅ መገኛዋ ኢትዮጵያ፣ በአፍሪካውያን መሰባሰቢያ አዲስ አበባ፣16ኛውን የአፍሪካ የሥጋት መከላከል ዐቅም ጉባኤ (ARC-COP16) በይፋ አስጀምረናል ብለዋል።   አህጉራችን በአየር ንብረት ለውጥ ክፉኛ እየተፈተነች ትገኛለች ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፤ ሆኖም ይህ ፈተና ተስፋችንን የሚያጨልም፣ ጉዟችንን የሚገታ አይሆንም ሲሉም ገልጸዋል። በእልህ፣ በቁጭትና በእንችላለን ኅብረት አንድነታችንን የምናጠናክርበት አጋጣሚ ነው። እኛ አፍሪካውያን ከአደጋ በኋላ ለሚመጣ ርዳታ እጅ ከመዘርጋት ይልቅ፣ አደጋን ቀድሞ መከላከልና በሳይንሳዊ መንገድ ለመፍትሔ መዘጋጀት የህልውናችን መሠረት ሊሆን ይገባል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ በዚህ ረገድ ራዕይ ሰንቃ፣ ክንዷን አበርትታ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ዐቅም እየገነባች መሆኑን ገልጸው፤ በአረንጓዴ ዐሻራ የምድርን ገጽታ እየቀየርን መሆኑንም ተናግረዋል። በምግብ ሉዓላዊነት ንቅናቄ ራሳችንን ለመቻል እየተጋን ነው። በታዳሽ ኃይል ልማትም የአህጉራዊ ትሥሥር ገመድ እየሆንን ነው ብለዋል። ሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች በበዙበት፣ በአንጻሩ ዓለም አቀፋዊ ድጋፎች በቀነሱበት በዚህ ወቅት፣ የአፍሪካ ሥጋትን የመከላከል ዐቅም (African Risk Capacity-ARC) የመሰሉ አህጉራዊ ተቋሞቻችንን ማጠናከር አማራጭ የሌለው ጉዳይ መሆኑንም ገልጸዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው የአደጋ ሥጋትን በጥናት መለየት፣ ቀድሞ መከላከል፣ ችግር ሲከሠትም በአፍሪካዊ ዐቅም ምላሽ መስጠት ይገባል። ኢትዮጵያም ለዚህ የአፍሪካውያን ሌላኛው የሉዓላዊነት ግብ መሳካት በአርአያነት ትተጋለች ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም