አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በኢሉባቦር ዞን በክረምቱ ወቅት የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ስራ እየተከናወነ ነው
Dec 2, 2025 222
መቱ ፤ሕዳር 23/2018 (ኢዜአ)፡-በኢሉባቦር ዞን በክረምቱ አረንጓዴ አሻራ መርሐግብር የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ስራ በዘመቻ መልክ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የዞኑ የተለያዩ ሴክተር መስሪያ ቤቶች ሰራተኞች የተሳተፉበት በክረምቱ ወቅት የተተከሉ ችግኞችን በጋራ እየተንከባከቡ ናቸው። የኢሉባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አወል መሐመድ በዞኑ በክረምቱ ወራት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መተከላቸውን አስታውሰዋል። የችግኞቹን የጽድቀት መጠን ለማሳደግም ህብረተሰቡ እንክብካቤ እንዲያደርግ ግንዛቤ በመፈጠሩ የዞኑ የመንግስት ሰራኞችን ጨምሮ ሁሉንም የሕብረተሰብ ክፍሎች ባሳተፈ መልኩ እንክብካቤው በዘመቻ መልክ እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህም የጽድቀት መጠናቸው በአሁኑ ወቅት ከ95 በመቶ በላይ መድረሱን ተናግረዋል። ለችግኞቹ የሚደረገው እንክብካቤ ጽድቀታቸውን ከማረጋገጥ ባለፈ በአጭር ግዜ ደርሰው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸው እንዲጎላ እንደሚያግዝም አመልክተዋል። በችግኝ እንክብካቤው ከተሳተፉ የመንግስት ሰራተኞች መካከል የዞኑ የፐብሊክ ሰርቪስና ሰው ሀብት ልማት ጽሕፈት ቤት ባለሞያ አቶ መላኩ ከበደ በበኩላቸው በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር በአንድነት የተከልናቸውን ችግኞች በአንድነት የመንከባከብ ስራ እየሰራን ነው ብለዋል። በመንግስት አገልግሎት ለህዝብ ከሚሰጧቸው አገልግሎት ባለፈ በክረምቱ ወራት በበጎ ፈቃድ አገልግሎት የተከሏቸውን ችግኞች በመንከባከብ እንዲጸድቁ ለማድረግ በስፍራው መገኘታቸውን ገልጸዋል። በአረንጓዴ አሻራ የተከልሏቸው ችግኞች የሚጠበቀውን ውጤት ለማግኘት መትከል ብቻውን በቂ ባለመሆኑ የእንክብካቤ ስራውን ማጠናከር በማስፈለጉ ለዚሁ ተግባር መጥቻለሁ ያሉት ደግሞ ወይዘሮ ፋጡማ የሱፍ ናቸው። አቶ እንዳሻው ጆቴ በበኩላቸው የተተከሉ ችግኞችን በጋራ በመንከባከብ ለውጤት ለማብቃት ያልተቋረጠ ክትትል በማስፈለጉ በተከላ ወቅቱ የገቡትን ቃል በተግባር ለማዋል ስራው ላይ መገኘታቸውን ጠቁመዋል። በክረምቱ የተተከሉት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተገቢው እንክብካቤ ካልተደረገላቸው በመጥፋት የወጣባቸው ከፍተኛ ገንዘብ ለብክነት እንደሚዳረግም አክለዋል።
ኢትዮጵያውያን የደመቁበት የኢጋድ የሚዲያ አዋርድ
Dec 1, 2025 234
ሶስተኛው የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት ህዳር 20 እና 21 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የሽልማት ስነ ስርዓቱ “ውጤታማ የአየር ንብረት ዘገባ ደህንነቱ ለተረጋገጠ፣ ጠንካራ እና የተረጋጋ ቀጣና” በሚል መሪ ሀሳብ ተከናውኗል። ኢጋድ ቀጣናዊ ሁነቱን ያዘጋጀው ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በመተባበር ነው። ፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ የሽልማት መርሃ ግብሩ የሚዲያ አጋር ሲሆን የሁለት ቀኑን የሽልማት መርሃ ግብር የቀጥታ ስርጭት ሽፋን በመስጠት ለመላው አፍሪካውያን ተደራሽ አድርጓል። የአፍሪካ ኢምፖርት እና ኤክስፖርት ባንክ(አፍሪኤግዚም ባንክ) ለፕሮግራሙ ድጋፍ አድርጓል። የኢጋድ የሚዲያ አዋርድ ተሳታፊ የሚዲያ ባለሙያዎች ፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያን ጎብኝተዋል። የ2025 የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት በ10 ዘርፎች ተከናውኗል። የህትመት ጋዜጠኝነት፣ የሬዲዮ ጋዜጠኝነት፣ የቴሌቪዥን ጋዜጠኝነት፣ ዲጂታል ሚዲያ፣ ፎቶግራፈር፣ ሀገር በቀል ዘገባ፣ የዓመቱ ተጽእኖ ፈጣሪ/ የይዘት ቀራጭ፣ የማህበራዊ ሚዲያ ተጽእኖ ፈጣሪዎች እና የእድሜ ዘመን ሽልማት የሽልማት ዘርፎቹ ናቸው። 400 የሚሆኑ የኢጋድ አባል ሀገራት የሚዲያ ባለሙያዎች ስራዎቻቸውን ያስገቡ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 94 የሚሆኑት ኢትዮጵያውያን የሚዲያ ባለሙያዎች መሆናቸውን ኢጋድ አስታውቋል። ከ94ቱ ኢትዮጵያውያን የሚዲያ ባለሙያዎች መካከል ሶስቱ በተለያዩ ዘርፎች ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋዜጠኛ ጌትነት ሸንቁጤ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የ2025 የሚዲያ ሽልማት በዲጂታል ሚዲያ ዘርፍ አሸናፊ በመሆን ሽልማቱን ተቀብሏል። ጋዜጠኛ ጌትነት ሸንቁጤ ሽልማቱን የተጎናጸፈው “Climate Intelligence for Survival: IGAD’s Push for Accurate, Actionable Data” በሚል ርዕስ በጻፈው ጽሁፍ ነው። የጋዜጠኛ ጌትነት ጽሁፍ በኢጋድ ቀጣና ያለውን የአየር ንብረት ለውጥ ፈተና የሚዳስስ ነው። በተደጋጋሚ ጊዜ የሚከሰት ድርቅ፣ የጎርፍ አደጋዎችና ኢ-ተገማች የአየር ጸባይ ለውጦች ዜጎችን በማፈናቀል እና በቁም እንስሳት ላይ ያደረሱትን ጉዳት ይቃኛል። ትክክለኛ፣ ጊዜውን የጠበቀና ለተግባር ምላሽ የሚያገለግሉ የአየር ንብረት መረጃዎች የማይበገር አቅም ለመገንባትና አደጋዎችን ለመከላከል ያላቸውን ሚናም ተዳሷል። በጽሁፉ ላይ የኢጋድ የአየር ንብረት ትንበያና ትግበራ ማዕከል(ICPAC) የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓትን በማጠናከር፣ የትንበያ አቅም ማሳደግና የረጅም ጊዜ የአየር ንብረት የመቋቋም አቅም ላይ እያከናወነ ያለው ስራ ተቀምጧል። የአየር ንብረት ለውጥ ፈተናዎች፣ የአንበጣ መንጋ፣ ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብና ሌሎች ፈተናዎችን ለመከላከል ተአማኒነት ያለው የአየር ንብረት መረጃ ወሳኝ መሆኑም ተመላክቷል። በተለይም ኑሯቸው በተለያዩ ወቅቶች ላይ ለተመረኮዙ አርሶ እና አርብቶ አደሮች መረጃው ወሳኝ መሆኑን ያስቀምጣል። ሌላኛው ተሸላሚ የኦሮሚያ ብሮድካስቲንግ ኔትወርክ (ኦቢኤ) ጋዜጠኛ ሽመክት ጉግሳ ነው። የተሸለመበት ዘርፍ በኦሮምኛ ቋንቋ በሰራው ፕሮግራም ነው። ፕሮግራሙ ዛፎች ከሰው ህይወት ጋር ያላቸውን ቁርኝት በዋናነት ይቃኛል። መንደርደሪያውን ከዓለም የዛፍ ጠቀሜታና ጥበቃ በማድረግ በኦሮሚያ ክልል እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችን ይዳስሳል። ዛፍ መትከል ተፈጥሮና የሰው ልጅን እንዴት እንደሚጠብቅ በተቃራኒው መቁረጥ የሚያደርሰውን ጉዳትም ያስቃኛል። የ21 ደቂቃ ፕሮግራሙ የኦሮሞ ህዝብ በዘመናት መካከል ዛፎችና የደን ሀብቶች እንዲጠበቁ ያደረገው አስተዋጽኦ ተወስቶበታል። በተለይም በገዳ ስርዓት ውስጥ ዛፍን መጠበቅ ያለው ሚና በስፋት ተነስቷል። አንድ ዛፍ ለአራት ሰዎች መኖር መሠረት ይሆናል፤ ዛፍ መቁረጥ አራት ሰዎችን እንዲሞቱ ያደርጋል የሚል የአባገዳ አስተያየትም ተጠቃሽ ነው። አባ ገዳዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ እናቶችና የአካባቢ ማህበረሰቦች ተፈጥሮን ጠብቆ በማቆየት ያላቸው ሚና ቁልፍ እንደሆነ ተመላክቷል። የሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ራዲዮ መስራችና ስራ አስኪያጅ አንጋፋዋ ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩም የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለስልጣን(ኢጋድ) የህይወት ዘመን ጋዜጠኝነት ሽልማት ተበርክቶላታል። ጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ በሬዲዮ ጋዜጠኝነት ግንባር ቀደምና በዘርፉ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቷንም ኢጋድ ገልጿል። በብሮድካስት ሚዲያው ከ40 ዓመት በላይ የቆየችው ጋዜጠኛ መዓዛ ሸገር ኤፍኤም 102.1ን ከ18 ዓመታት በፊት በማቋቋም በኢትዮጵያ ቀዳሚ የመረጃ እና የመዝናኛ ጣቢያ እንዲሆን ማድረጓ አመልክቷል። ከጋዜጠኛ መዓዛ ብሩ አበይት ፕሮግራሞች መካከል “ማንን ምን እንጠይቅልዎ?” እና “ሸገር ካፌ” ተጠቃሽ ናቸው። ጋዜጠኛዋ በፕሮግራሞቹ ህዝብን ከመንግስት አገልግሎቶች ጋር በማገናኘትና በማህበራዊ፣ የህግ እና የፖለቲካ ጉዳዮች ላይ ሀሳብ ላይ የተመረኮዙ ውይይቶች እንዲካሄዱ መድረክ መፍጠር መቻሏንም ነው የገለጸው። የሸገር ኤፍ ኤም 102.1 ራዲዮ መሪ ሀሳብ በሆነው የእናንተ ሬዲዮ መዓዛ በጋዜጠኝነት ሙያ ህዝብን ለማገልገልና የኢትዮጵያውያንን ድምጽ ለማጉላት ያላትን ቁርጠኝነት ኢጋድ አድንቋል። ሽልማቱ በቀጣናው ገንቢ ሚና ያለው ጋዜጠኝነት እንዲጎለብት አዎንታዊ ሚና እንደሚጫወትም ኢጋድ አመልክቷል።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት ወደ ሀገሪቱ የሚነፍሰው ደረቅ እና ቀዝቃዛ አየር ተጠናክሮ ይቀጥላል
Dec 1, 2025 218
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አስር ቀናት ከሳይቤሪያ ከፍተኛ የአየር ግፊት ላይ በመነሳት ወደ ሀገሪቱ የሚነፍሰው ደረቅ እና ቀዝቃዛ አየር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለፀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንደገለፀው በሚቀጥሉት አሥር ቀናት ዝናብ ሰጭ የአየር ሁኔታ ክስተቶች በጋ ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት አካባቢዎች ላይ ቀጣይነት ይኖረዋል። ዝናብ ሰጭ የአየር ሁኔታ ክስተቶች በጥቂት የደቡብ እና የደቡብ ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች አልፎ አልፎ በሚኖሩት ቀናቶች ላይ በተዳከመ ሁኔታ ቀጣይነት ይኖራቸዋል። በዚህም የደቡብ ኦሮሚያ ዞኖች፤ የሲዳማ ክልል ዞኖች፤ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደቡባዊ ዞኖች እና የሶማሌ ክልል ደቡባዊ ዞኖች በጥቂት ስፍራዎቻቸው ላይ በጣም አነስተኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖራቸው አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች እንደሚጠቁሙ ገልጿል። በሌላ በኩል ከሚኖረው የደመና ሽፋን ላይ በመነሳት በጥቂት የሰሜን፣ መካከለኛውና ደቡብ ጎንደር ዞኖች፣ ባህርዳር ዙሪያ፣ አዊ ፣ በምዕራብና ምስራቅ ጎጃም አልፎ አልፎ በሚኖሩት ቀናት ወቅቱን ያልጠበቀ አነስተኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙም ትንበያው አብራርቷል። የምዕራብ ኦሮሚያ ክልል ዞኖች፣ አርሲ እና ምዕራብ አርሲ፤ ባሌ እና ምስራቅ ባሌ ዞኖች፣ ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ካማሺ እና የማኦኮሞ ልዩ ዞን፤ የጋምቤላ ክልል ዞኖች፣ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ዞኖችም አልፎ አልፎ ወቅቱን ያልጠበቀ አነስተኛ መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ። ስለሆነም በሚኖሩት ደረቅ ቀናቶች የደረሱ ሰብሎች መሰብሰብ አስፈላጊ መሆኑን ኢንስቲትዩቱ ጠቁሟል። በሌላ በኩል ከሳይቤሪያ ከፍተኛ የአየር ግፊት ላይ በመነሳት ወደ ሀገሪቱ የሚነፍሰው ደረቅ እና ቀዝቃዛ አየር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች እንደሚያሳዩም በመግለጫው ተብራርቷል። በዚህም የበጋው ደረቅ፣ ፀሐያማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ በተለይም በሰሜን፣ ምስራቅ፣ መካከለኛውና ደቡብ ደጋማ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ የለሊትና የማለዳው ቅዝቃዜ ከአምስት ዲግሪ ሴልሺየስ በታች እንደሚሆን ትንበያው ያሳያል።
የኢትዮጵያ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤን ለማስተናገድ መመረጥ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ላላት ቁርጠኝነት የተሰጠ ዕውቅና ነው
Nov 30, 2025 226
አዲስ አበባ፤ ህዳር 21/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤን ለማስተናገድ መመረጥ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ላላት ቁርጠኝነት የተሰጠ ዕውቅና መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) ገለጹ። የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል በሚደረግ ሂደት የሚዲያ ሚና ወሳኝ መሆኑንም ሚኒስትሩ ገልጸዋል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ''ውጤታማ የአየር ንብረት ዘገባ፤ ደኅንነቱ ለተረጋገጠ ጠንካራና የተረጋጋ ቀጣና” በሚል መሪ ሃሳብ የ2025 የሚዲያ ሽልማት በአዲስ አበባ በማካሄድ ላይ ይገኛል። በመድረኩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)፣ የኢጋድ ዋና ፀሀፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)፣ ቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል። ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ኢጋድ ከተመሰረተበት ጊዜ ጀምሮ ለቀጣናዊ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠት በትኩረት እየሰራ ነው ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስም በስትራቴጂክ ዕቅድ መምራት የሚያስችል የማስተባበር ሥራ እየሰራ አንደሚገኝ ገልጸዋል። ኢትዮጵያም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ በተግባር የተደገፈ ለውጥ አምጪ የመፍትሔ እርምጃዎች ላይ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች እንደምትገኝ ተናግረዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል ለጎረቤት ሀገራት ጭምር በማጋራት ውጤታማ ስራ ማከናወኗን አስረድተዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብም በአህጉሪቷ የታዳሽ ኃይል መስክ አዲስ ምዕራፍ በመክፈት የዲጂታል ሽግግር አንቀሳቃሽ ኃይል ለመሆን መብቃቱን አንስተዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ እና ሌሎች የታዳሽ ሀይል የልማት ስኬቶች ለአፍሪካ የኢንዱስትሪና የዲጂታል ሽግግር በምሳሌነት የሚወሰዱ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኢኮኖሚ ግንባታም 2ኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ በስኬት በማስተናገድ ቀርጠኝነቷን ለዓለም ማስመስከሯን ገልጸዋል። ከሁለት ዓመታት በኋላ የሚካሄደውን የመንግስታቱ ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤን (COP 32) በ2027 ለማስተናገድ በሙሉ ድምጽ መመረጧ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ላላት ቁርጠኝነት የተሰጠ እውቅና መሆኑን ተናግረዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመዋጋትም መገናኛ ብዙኃን ግንባር ቀደም ሚና እንዳላቸው የኢጋድ 2025 የጋዜጠኞች ዕውቅና ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ዋና ፀሀፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)፤ እያደገ የመጣው የመገናኛ ብዙኃን ሙያተኞች ሽልማት ቀጣናዊ ድምፆችን ለማጉላት ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። መገናኛ ብዙኃን ሙያተኞችም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ ሰላምና ደኅንነትን ለማስጠበቅ ወሳኝ ሚና እንዳላቸው አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም የቀጣናውን ማህበረሰብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያሻሽል ወሳኝ የልማት እርምጃ መሆኑን ገልጸዋል። በብራዚል ቤለም በተካሄደው 30ኛ ጉባኤ ላይ ከሁለት ዓመታት በኋላ የሚካሄደውን 32ኛ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤ (COP-32) ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ መመረጧ ይታወቃል።
ሶስተኛው የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው
Nov 30, 2025 163
አዲስ አበባ፤ህዳር 21/2018(ኢዜአ)፦የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የ2025 የሚዲያ ሽልማት በአዲስ አበባ ስካይ ላይት ሆቴል በመካሄድ ላይ ነው። የሽልማት ስነ ስርዓቱ “ውጤታማ የአየር ንብረት ዘገባ ደህንነቱ ለተረጋገጠ፣ጠንካራ እና የተረጋጋ ቀጣና” በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ያለው። በመድረኩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)፣ የኢጋድ ዋና ፀሀፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ፣ ከፍተኛ የመንግሥት አመራሮች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። ኢጋድ ቀጣናዊ ሁነቱን ያዘጋጀው ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በመተባበር ሲሆን ፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ የሽልማቱ ብቸኛ የሚዲያ አጋር ነው። በመርኃግብር በአፍሪካ ቀንድ ውጤታማ የአየር ንብረት ትርክትን ለቀረጹ ጋዜጠኞች እና የፊልም ባለሙያዎች እውቅና ይሰጣል። የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት ከእ.አ.አ 2023 ጀምሮ እየተካሄደ የሚገኝ ዓመታዊ ሁነት ሲሆን የ2023 ሽልማት በጅቡቲ የተካሄደ ሲሆን የ2024ቱ ደግሞ በኬንያ ናይሮቢ መካሄዱም ይታወሳል።
የአየር ንብረት ለውጥ በአፍሪካ ቀንድ አገሮች የእንስሳት ሃብት ላይ የሚያደርሰውን ተፅዕኖ ለመከላከል በቅንጅት መስራት ይገባል
Nov 30, 2025 133
አዲስ አበባ፤ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፦ የአየር ንብረት ለውጥ በአፍሪካ ቀንድ አገሮች የእንስሳት ሃብት ላይ የሚያደርሰውን ተፅዕኖ ለመቋቋም አፋጣኝና የተቀናጀ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ የዘርፉ ባለሙያዎች ገለፁ። ሶስተኛው የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) ሚዲያ አዋርድ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ መካሄድ የጀመረ ሲሆን፤ በዚህ መርሃ ግብር ፐልስ ኦፍ አፍሪካ (pulse of Africa) የሚዲያ አጋር ነው፡፡ የሽልማት ስነ ስርዓት መርሃ ግብር “ውጤታማ የአየር ንብረት ዘገባ ደህንነቱ ለተረጋገጠ፣ ጠንካራ እና የተረጋጋ ቀጣና” በሚል መሪ ሀሳብ የሚከናወን ነው። በመርሃ ግብሩ የሁለተኛ ቀን ውሎ "በታላቁ የአፍሪካ ቀንድ በአየር ንብረት መናጋት ዘመን የእንስሳት እርባታ" በሚል ርዕሰ ጉዳይ ላይ የፓናል ውይይት እየተካሄደ ነው። የፓናሉ ተሳታፊዎቹ በአየር ንብረት ለውጥ የሚከሰት የተራዘመ ድርቅ ፣ የሙቀት መጨመርና ወረርሽኝ በእንስሳት ሃብት ላይ መጠነ ሰፊ ተፅዕኖ እያሳደረ መሆኑን አንስተው፤ ይህም በቀጣናው የምግብ ዋስትናን ላይ ተግዳሮት መደቀኑን ጠቅሰዋል። በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት በአፍሪካ ቀንድ አገሮች የእንስሳት ሃብት ላይ የሚደርሰውን ተፅዕኖ ለመቋቋም አፋጣኝና የተቀናጀ እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ የዘርፉ ባለሙያዎች አሳስበዋል። በኢጋድ የአየር ንብረት ትንበያና አፕሊኬሽኖች ማዕከል የአየር ንብረት ሞዴሊንግ ባለሙያ ታምራት በቀለ (ዶ/ር) ፤ እየጨመረ የመጣውን የአየር ንብረት ለውጥና በእንስሳት ጤና ላይ የደቀነውን ስጋት ለመከላከል አስቸኳይ እርምጃ መውሰድ ይገባል ብለዋል። በቀጣናው የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የሚያስችሉ መፍትሄዎችን መተግበር ወሳኝ መሆኑንም ባለሙያ ታምራት በቀለ (ዶ/ር) ተናግረዋል። ሙቀትን የሚቋቋም መኖ እና የተሻሻሉና የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋሙ የእንስሳት ዝርያዎችን ማስተዋወቅ እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት ። በዓለም አቀፍ የእንስሳት ምርምር ተቋም ከፍተኛ ሳይንቲስት በርናርድ በት በበኩላቸው፤ የክትባት ሽፋን በከፍተኛ ሁኔታ ማስፋፋትና ጠንካራ የበሽታ ቁጥጥር ስርዓት መዘርጋት አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰዋል። የአየር ንብረት ተጽዕኖን ለመቋቋም ጥናትና ምርምርን ማጠናከር እንደሚገባ የኢጋድ የእንስሳት እርባታ አካባቢዎች እና የእንስሳት ልማት ማዕከል የደረቅ መሬት ልማት ክፍል ኃላፊ ጉያ ሮባ ተናግረዋል። የአየር ሁኔታ ለውጦችን እና ሊከሰቱ የሚችሉ ድርቆችን አስቀድመው የሚጠቁሙ መረጃዎችን ለህብረተሰቡ ተደራሽ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑንም አስገንዝበዋል።
ከኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ኢንስቲትዩት የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
Nov 29, 2025 189
በአሁን ወቅት በአፋር ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በኤርታሌ አካባቢ ልዩ ቦታው ሃይሊ ጉብ በተባለ ስፍራ የተከሰተውን የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ (Volcanic Eruption) አስመልክቶ በማዕድን ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ኢንስቲትዩት የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ የኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ኢንስቲትዩት የተለያዩ የስነ ምድር የምርምር ስራዎችን እየሰራ የሚገኝ የምርምር ተቋም ሲሆን የስነ-ምድር አደጋዎችንም የማጥናት ተልኮ እንዳለው ይታወቃል፡፡ ይሀንን ምርምር ለመከወንም ሃገር ውስጥና ከሃገር ውጭ ካሉ የተለያዩ የመንግስት መስሪያ ቤቶች እና ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር በጋራ በመሆን እየሰራ ይገኛል፡፡ በአሁን ወቅት በአፋር ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በኤርታሌ አካባቢ ልዩ ቦታው ሃይሊ ጉብ በተባለ ስፍራ ሀዳር 14/2018 ዓ.ም ጠዋት አራት ሰዓት አካባቢ የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ(Volcanic Eruption) እንደተከሰተ ይታወቃል። ይህ የእሳተ ገሞራ ፈንዳታ ከመከሰቱ በፊት ከሃምሌ 2017 ዓ.ም ጀምሮ የተለያዩ ለእሳተ ገሞራ ፍንዳታ መከሰት አመላካች ምልክቶችን በቅርበት የመከታተል፣ መረጃዎችን የማሰባሰብና መረጃዎችን የመስጠት ስራ ሲሰራ ቆይቷል፡፡ አሁን ላይ የእሳተ ገሞራ ፍንዳታው ያለበትን ሁኔታ የሚመለከትና የሚያጠና የጥናት ቡድን ተቋቁሞ ወደ ቦታው በመላክ ጥናት እያደረገ የሚገኝ ሲሆን አሁን በቦታው ላይ ያለው ሁኔታ በአንጻራዊነት የተረጋጋ ስለሆነ ማሀበረሰቡ ተረጋግቶ ስራውን እንዲያከናውን እያሳሰብን በሃገር ውስጥና ከሃገር ዉጭ ካሉ ተቋማትና ተመራማሪዎች ጋር በጋራ እየተሰራ ያለው የምርምር ስራ ሲጠናቀቅ ተጨማሪ መግለጫ የምንሰጥ ይሆናል፡፡ የኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢጃራ ተስፋዬ አዲስ አበባ፡ ኢትዮጵያ
ኢትዮጵያ ለሌሎች ሀገራት ምሳሌ የሆኑ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ተግባራትን እያከናወነች ነው
Nov 29, 2025 108
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 20/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ምላሽና መከላከል ለሌሎች ሀገራት ምሳሌ የሆኑ ተግባራትን እያከናወነች እንደምትገኝ በኢትዮጵያ የኢጋድ ተጠሪ አበባው ቢሆነኝ ገለፁ። ሦስተኛው የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) የሚዲያ ሽልማት መርኃ ግብር በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል፡፡ በኢትዮጵያ የኢጋድ ተጠሪ አበባው ቢሆነኝ በዚሁ ወቅት፤ የ2025 የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት በተለያዩ መርሐ ግብሮች ይካሄዳል ብለዋል፡፡ በዛሬው ዕለት የቀጣናው ሀገራት በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ የሚያከናውኗቸውን ተግባራት በሚመለከት የባለድርሻ አካላት ፓናል ውይይቶች፣ የልምድ ልውውጥና የጉብኝት መረሃ ግብሮች እየተካሄዱ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ቅነሳና መከላከል ዙሪያ እያከናወነች ያለው ተግባር በእጅጉ የሚበረታታና ለሌሎች ሀገራትም ሁነኛ ምሳሌ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ውጤታማ ተግባራት የቀጣናውና የአፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠት በቁርጠኝነት እንዲሰሩ መነሳሳትን እንደሚፈጥርም ጠቁመዋል፡፡ የኢጋድ አባል ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን ተፅእኖ ቀድሞ መከላከል የሚያስችል አቅም መገንባት ላይ ትብብራቸውን ማጠናከር እንደሚገባቸው አመላክተዋል። የሚዲያ ሽልማት መርሃ ግብሩ ከውድድር ባለፈ በኢጋድ ቀጣና እና በአህጉሪቱ በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ የሚያጋጥሙ ውስብስብ ችግሮችንና ተግባራዊ መፍትሔዎችን ለማመላከት የሚረዳ ስለመሆኑ ተናግረዋል። እነዚህና መሠል የጋራ ትብብርን የሚያጠናክሩ ተግባራትን በማስቀጠል በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ቅነሳና የመከላከል ሥራዎችን በትኩረት ማጠናከር ይገባል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በቀጣናው የንጹህ ኢነርጂ ማዕከል የሚያደርጋትን የአረንጓዴ ልማት እንቅስቃሴ እያደረገች ነው
Nov 29, 2025 134
አዲስ አበባ፤ ህዳር 20/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በቀጣናው የንጹህ ኢነርጂ ማዕከል የሚያደርጋትን የአረንጓዴ ልማት እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኑን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ፡፡ ሶስተኛው የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት(ኢጋድ) ሚዲያ አዋርድ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ መካሄድ የጀመረ ሲሆን፤ በዚህ መርሃ ግብር ፐልስ ኦፍ አፍሪካ(pulse of Africa) የሚዲያ አጋር ነው፡፡ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ ኢጋድ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን በመቋቋም ዙሪያ ግንዛቤ መፍጠር የሚያስችል የሚዲያ አዋርድ በማዘጋጀቱ የላቀ ምስጋና ይገባዋል፡፡ የኢጋድ ሚዲያ አዋርድ ቀጣናዊ ትብብርን በማጠናከር የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም መሳኝ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ የአፍሪካን ነባራዊ ሁኔታ እየቀየረ መሆኑን በማንሳት፤ ድርቅ፣ ያልተጠበቀ ዝናብ፣ ጎርፍና ከፍተኛ ሙቀት በአህጉሪቱ ገሀድ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በተለይም በአርብቶና ከፊል አርብቶ አደር አካቢዎች፣ በዝቅተኛ ስፍራዎች የዜጎችን ህይወት እየፈተነ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ ዝቅተኛ አስተዋጽኦ ቢኖራትም ከፍተኛ ተጎጂ መሆኗን አንስተው፤ ችግሩን ለመፍታት የጋራ ጥረት ይጠይቃል ብለዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ስርዓት፣ ፈጠራን መሰረተ ያደረገ የታዳሽ ኃይል ልማት፣ ማህበረሰብ ተኮር የማገገሚያ ስልቶችን መጠቀም እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡ ከዚህ አኳያ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በሰባት ዓመታት ውስጥ ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን መትከሏን አስታውሰዋል፡፡ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን ጨምሮ ከእንፋሎት፣ ከፀሀይና ከንፋስ የታዳሽ ኃይል ልማት ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያ በቀጣናው የንጹህ ኃይል ማዕከል የሚያደርጋትን የአረንጓዴ ልማት እንቅስቃሴ እያደረገች መሆኑን ጠቁመው ይህም ለጎረቤት ሀገራት ኃይል በማቅረብ ቀጣናዊ ትብብርና ትስስርን ለማጠናከር የጎላ አበርክቶ አለው ነው ያሉት፡፡ ኢጋድ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስትራቴጂ በመንደፍ ለዜጎች የበለጸገ ነገን ለማስተላለፍ በሚደረገው ጥረት ሚናውን እየተወጣ መሆኑን አንስተዋል፡፡ የኢጋድ ሚዲየ አዋርድ ለጋዜጠኞች እውቅና በመስጠት የሚዲያን አቅም እንደሚያሳደግ ገልጸው፤ የዘመኑን አንገብጋቢ የአየር ንብረት ለውጥ ለመቋቋም በጋራ መስራት እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡ በኢትዮጵያ የኢጋድ ተጠሪ አበባው ቢሆነኝ እንደገለጹት፤ በመርሃ ግብሩ የቀጣናው ሀገራት በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ የሚያከናውኗቸውን ተግባራት የሚመለከት ምክክርና ጉብኝት ይካሔዳል። ኢትዮጵያ በቀጣናዊ ትብብር፣ በሰላም ግንባታ፣ በአረንጓዴ ልማትና በመሰረተ ልማት ግንባታ ያሳየችው እመርታ በሳል አመራር እንዳላት የሚያመላክት ስለመሆኑ ነው የገለጹት። ይህም ለኢጋድ አባል አገራት ትልቅ ኩራት ከመሆን ባለፈ ኢትዮጵያ ለቀጣናው ሀገራት ምሳሌ የሆነ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ተግባራትን እያከናወነች መሆኑን ያመለክታል ብለዋል። አዲስ አበባ ሶስተኛው የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት(ኢጋድ) ሚዲያ አዋርድ እንድታዘጋጅ መመረጧ ለአባል ሃገራቱ ትልቅ መነሳሳትን የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል።
ሶስተኛው የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት ዛሬ እና ነገ በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Nov 29, 2025 140
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 20/2018 (ኢዜአ)፡- የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የ2025 የሚዲያ ሽልማት ዛሬ እና ነገ በአዲስ አበባ ስካይ ላይት ሆቴል ይደረጋል። የሽልማት ስነ ስርዓቱ “ ውጤታማ የአየር ንብረት ዘገባ ደህንነቱ ለተረጋገጠ፣ ጠንካራ እና የተረጋጋ ቀጣና” በሚል መሪ ሀሳብ የሚከናወን ነው። ኢጋድ ቀጣናዊ ሁነቱን ያዘጋጀው ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በመተባበር ነው። ፐልስ ኦፍ አፍሪካ ሚዲያ የሽልማቱ ብቸኛ የሚዲያ አጋር ነው። የአፍሪካ ኢምፖርት እና ኤክስፖርት ባንክ (አፍሪኤግዚም ባንክ) ለፕሮግራሙ ድጋፍ እንደሚያደርጉም አስታውቋል። የዚህ ዓመት ሽልማት በአፍሪካ ቀንድ ውጤታማ የአየር ንብረት ትርክትን ለቀረጹ ጋዜጠኞች እና የፊልም ባለሙያዎች እውቅና የሚሰጥ ነው። የሁለት ቀን ሁነቱ የአየር ንብረት ጠንካራ ዘገባዎች እና ሀሳቦች የሚቀርቡበት እንዲሁም ቀጣናዊ ትብብር ጎልቶ የሚታይበት መሆኑን ኢጋድ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል። የ2025 የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት በ10 ዘርፎች የሚከናወን ነው። የህትመት ጋዜጠኝነት፣ የሬዲዮ ጋዜጠኝነት፣ የቴሌቪዥን ጋዜጠኝነት፣ ዲጂታል ሚዲያ፣ ፎቶ ግራፈር፣ ሀገር በቀል/ ብሄራዊ ቋንቋ ዘገባ፣ የዓመቱ ተጽእኖ ፈጣሪ/ የይዘት ቀራጭ፣ የማህበራዊ ሚዲያ ተጽእኖ ፈጣሪዎች እና የእድሜ ዘመን ሽልማት የሽልማት ዘርፎቹ ናቸው። የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት ከእ.አ.አ 2023 ጀምሮ እየተካሄደ የሚገኝ ዓመታዊ ሁነት ነው። የ2023 ሽልማት በጅቡቲ፣ የ2024ቱ በኬንያ ናይሮቢ መካሄዱም ይታወሳል።
የኢትዮጵያ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤን ለማስተናገድ መመረጥ የታዳሽ ኃይል ልማት ቁርጠኝነቷን የሚያረጋግጥ ነው
Nov 28, 2025 177
አዲስ አበባ፤ ህዳር 19/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት(COP-32) ጉባኤ ለማስተናገድ መመረጥ ለታዳሽ ኃይል ልማት ትግበራ ቁርጠኝነቷን የሚያረጋግጥ መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሃብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) ገለጹ። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሃብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ በሁሉም የታዳሽ ኃይል አማራጭ ዕምቅ የመልማት አቅም አላት። በኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ግንባታም የውሃ፣ የፀሐይ፣ የነፋስ፣ ጂኦተርማልና መሰል የኃይል አማራጮች ወሳኝ ሚና እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል። በገጠር አካባቢ የሚኖሩ ዜጎችን በፀሐይ ኃይል የኤሌክትሪክ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ እንደሚገኝም ተናግረዋል። የኤሌክትሪክ ኃይል ባልተዳረሰባቸው የገጠር መንደሮችና ከተሞች የፀሐይ ኃይል ተጠቃሚነት ለማሳደግ ከልማት አጋሮች ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ልማት ስኬትም የካርቦን ልቀትና የአየር ንብረት ለውጥ ስጋትን በመቀነስ ዓለም አቀፍ እውቅና እያስቸራት መሆኑን አብራርተዋል። የበለጸጉ ሀገራት ዕድገታቸውን ለማረጋገጥ የተጓዙበት መንገድ በካይ ጋዞችን በመጠቀም በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ዓለምን ዋጋ እያስከፈሉ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በኢትዮጵያ የሚገነቡ የታዳሽ ኃይል አማራጭ መሠረተ ልማቶችም በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ እየተፈተነ ለሚገኘው ዓለም ከፍተኛ ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን ጠቅሰዋል። የታዳሽ ኃይል መሠረተ ልማት ግንባታም የኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ወሳኝ ሚና እየተወጣ እንደሚገኝ አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል አማራጭ ልማት ቀጣናዊ የኃይል ትስስርን በማጠናከር ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ጉባኤዎችን የምታስተናግድበትን ዕድል መፍጠሩን አስረድተዋል። በብራዚል በተካሄደው መድረክ ኢትዮጵያ ኮፕ-32 ጉባኤን ለማስተናገድ ስትመረጥ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት ያስመዘገበችው ስኬት ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ኮፕ-32 ጉባኤን ለማስተናገድ መመረጧ በታዳሽ ኃይል አማራጭ፣ አረንጓዴ ዐሻራ እና በታዳሽ ኃይል ልማት ላስመዘገበችው ስኬት ዕውቅና የሚሰጥ መሆኑንም ሚኒስትሩ ተናግረዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርም የኢትዮጵያ የውሃ ሃብቶችን ደኅንነት በመጠበቅና የኃይል ማመንጫ ግድቦችን ከደለል በመታደግ ወሳኝ ድርሻ እየተጫወተ ነው ብለዋል። በብራዚል ቤለም በተካሄደው 30ኛ ጉባኤ ላይ ከሁለት ዓመታት በኋላ የሚካሄደውን 32ኛ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤ (COP-32) ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ መመረጧ ይታወቃል።
በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተተከሉ ችግኞች በተደረገ እንክብካቤ የጽድቀት መጠንን ማሳደግ ተችሏል
Nov 28, 2025 134
ደብረ ማርቆስ ፤ ሕዳር 19/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ባለፈው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ለተተከለው ችግኝ የእንክብካቤ ስራ እየተካሄደ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የተፈጥሮ ሃብት ቡድን መሪ አቶ ንጉሴ ሽመልስ ለኢዜአ እንደገለጹት የሚተከሉ ችግኞችን የጽድቀት መጠን በመጨመር የደን ሽፋኑን ለማሳደግ የእንክብካቤ ስራ እየተሰራ ነው። በዚህም ባሳለፍነው ክረምት ከተተከለው ከ219 ሚሊዮን በላይ ችግኝ ውስጥ 87 በመቶ የሚሆነው መጽደቅ መቻሉን ገልጸዋል። በዚህ ዓመት የተመዘገበው የችግኝ ጽድቀት መጠን ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከሰባት በመቶ በላይ ብልጫ እንዳለው ተመልክቷል። ከ500 ሺህ በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ ችግኞችን በማረም፣ በመኮትኮት፣ ውሃ በማጠጣትና ከእንስሳት ንክኪ ነጻ በማድረግ በተሰራው ስራ የጽድቀት መጠኑ እንዲጨምር ማስቻሉን ተናግረዋል። በዞኑ የአነደድ ወረዳ የጉዳለማ ቀበሌ ነዋሪ አቶ መንግስቱ ስሜነህ እንዳሉት፤ በአረንጓዴ ልማቱ የተተከሉ ችግኞች የመሬታቸውን ለምነት በመጨመር ምርታማነታቸው እንዲያድግ እያደረገ ነው። ይሄን በመገንዘብም ዘንድሮ የተተከሉ ችግኞች እንዲጸድቁ ለማድረግ በመጠበቅና በመንከባከብ የድርሻቸውን እየተወጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የደጀን ወረዳ የሽንቡሪ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አንዷለም አምሳሉ በበኩላቸው ፤ በየዓመቱ የሚተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ የጽድቀት መጠኑ እንዲጨምር እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የተተከሉ ችግኞች የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ ማድረጋቸውን ጠቁመው በቀጣይም ችግኞችን የመትከልና የመንከባከብ ስራን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ የተሰሩ ተግባራት የዞኑን የደን ሽፋን ባለፈው ዓመት ከነበረበት ከ17 ነጥብ 4 በመቶ ወደ 18 ነጥብ 1 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤን እንድታዘጋጅ መመረጧ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ለሰራቻቸው ውጤታማ ሥራዎች የተሰጠ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ነው
Nov 27, 2025 200
አዲስ አበባ፤ሕዳር 18/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤን እንድታዘጋጅ መመረጧ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ለሰራቻቸው ውጤታማ ሥራዎች ዳግም የተሰጠ ዓለም አቀፍ ዕውቅና መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው ዋና ዋና የዲፕሎማሲ ስራዎችን አስመልክተው ለመገናኛ ብዙሀን መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም ኢትዮጵያ ጉባኤውን እንድታዘጋጅ መመረጧ በአረንጓዴ ልማት፣ በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ማበረታቻ፣ በአረንጓዴ ዐሻራ እና መሰል የአየር ንብረት ጥበቃ ሥራዎች ላይ እያከናወነች ለሚገኙ ተግባራት የተሰጠ እውቅና ነው። ኢትዮጵያ የኮፕ-32 አስተናጋጅ ሆና መመረጧ በዲፕሎማሲው መድረክ ያላት ተሰሚነት ወደ ላቀ ደረጃ እየተሸጋገረ ለመምጣቱ ትልቅ ማሳያ መሆኑንም ጠቁመዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ (ዶ/ር) የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ (ኮፕ-32) ተወካይ ፕሬዝዳንት ሆነው መመረጣቸውንም ተናግረዋል። ጉባኤው ኢትዮጵያ አጀንዳዎቿን ለዓለም የምታስተዋውቅበት ትልቅ መድረክ እንደሚሆንም አምባሳደሩ ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው የቡድን-20 ጉባኤ ላይ በመሳተፍ የዲፕሎማሲ ስኬት ማስመዝገቧን ጠቅሰዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጉባኤው ባደረጉት ንግግር የአፍሪካን ሁነኛ አጀንዳዎችን ማንጸባረቃቸውንም አስታውሰዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከተመድ፣ ከዓለም ባንክ፣ ከአፍሪካ ልማት ባንክ፣ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (IMF) እና ከተለያዩ ሀገራት መሪዎች ጋር ውጤታማ የጎንዮሽ ውይይቶችን ማድረጋቸውንና በርካታ ስምምነቶች መፈጸማቸውን ገልጸዋል። የማሌዥያና የሲንጋፖር ሀገራት መሪዎች የሥራ ጉብኝት ኢትዮጵያ ካላት ሁለገብ የልማት ጉዞ አንፃር ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ከሀገራቱ ጋር በነዳጅ፣ በታዳሽ ኃይል፣ በግብርና፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በስማርት ከተማ ልማት እና በሌሎችም ጉዳዮች ላይ ስምምነት መደረጉን አስታውቀዋል። በተሰሩ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ሥራዎች ምክንያት የተለያዩ ሀገራት ኤምባሲያቸውን በአዲስ አበባ የከፈቱ ሲሆን፣ ሌሎችም ለመክፈት መወሰናቸው በመግለጫው ተመላክቷል። በዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ መስክ የተከናወኑ ተግባራትን በተመለከተም፤ በሳውዲ አረቢያ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ ወደ 23 ሺህ የሚጠጉ ዜጎችን በቅርቡ ወደ ሀገር መመለስ እንደተቻለ ተመላክቷል። ኢትዮጵያ በብራዚል ቤለም በተካሄደው የዓለም የአየር ንብረት (COP-30) ጉባኤ ላይ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት (COP-32) ጉባኤ ለማስተናገድ መመረጧ ይታወቃል።
መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉና ለዱር እንስሳት ሀብት የሰጠው ትኩረት ለዱር እንስሳት ጥበቃ ምቹ መደላድል ፈጥሯል
Nov 27, 2025 164
አዲስ አበባ፤ህዳር 18/2018(ኢዜአ)፦መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉና ለዱር እንስሳት ሀብት የሰጠው ትኩረት ለዱር እንስሳት ጥበቃና ባለስልጣኑ ለሚያከናውነው ተግባር ምቹ መደላድል መፍጠሩን የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ ገለፁ። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ በትናንትናው እለት በለንደን በተካሄደው በአፍሪካ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ የሚሰጠው ፕሪንስ ዊሊያም አዋርድ የ2025 አሸናፊ ሆነዋል። ዋና ዳይሬክተሩ አሸናፊ የሆኑት ተስክ ጥበቃ ሽልማት 2025 በተዘጋጀው በአፍሪካ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ የላቀ ድርሻና አስተዋፅኦ ላበረከቱ ሰዎች በሚሰጠው የህይወት ዘመን አበርክቶ ሽልማት ዘርፍ ነው። አቶ ኩመራ በዱር እንስሳት ጥበቃ ዘርፍ ከባለሙያነት እስከ ዋና ዳይሬክተርነት ከ30 ዓመት በላይ ያገለገሉ ሲሆን በዘርፉ በተለያዩ የጥናት እና ምርምር እንዲሁም የአስተዳደር ሥራዎች ላይ ያበረከቱት የላቀ አስተዋጽኦ ሽልማቱን ለማሸነፍ አስችሏቸዋል። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ እንዳሉት ባለስልጣኑ የዱር እንስሳትና መኖሪያ አካባቢያቸው በአግባቡ ተጠብቆና ለምቶ በዘላቂነት ጥቅም ላይ ለማዋል እየሰራ ይገኛል። የጥበቃ ቦታዎችን በጥናት ለይቶ በህብረተሰቡ ተሳትፎ ማቋቋም እንዲሁም የአስተዳደር ስርዓት ዘርግቶ በአግባቡ እንዲጠበቁና እንዲለሙ የማድረግ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። ባለስልጣኑ የዱር እንስሳት መጠለያ፣ የስፖርታዊ አደን የሚካሄድባቸው ጥበቃ ቦታዎችን ጨምሮ በተለያዩ ምድብ ያሉ የጥበቃ ቦታዎች በአግባቡ እንዲጠበቁ የማድረግ ስራም ያከናውናል ነው ያሉት። የጥበቃ ስራዎችን ከክልሎች፣ከማህበረሰቡ የሚመለከታቸው አካላት ጋር ከመስራት ባለፈ በዱር እንስሳት ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎችን ለመከላከል ከአገራት ጋር በመተባበር እንደሚሰራም ተናግረዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉና ለዱር እንስሳት ሀብት የሰጠው ትኩረት ለዱር እንስሳት ጥበቃና ባለስልጣኑ ለሚያከናውነው ተግባር ምቹ መደላድል መፍጠሩን ጠቁመዋል። ያገኙት ሽልማትም ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አለም አቀፍ እይታ እንዲያገኝ ለማስቻሉ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። ሽልማቱ ለዱር እንስሳት ጥበቃ የበለጠ ድምፅ ለመሆን፣ ህፃናት ለተፈጥሮ ሀብት ያላቸውን ተቆርቋሪነት ለማሳደግና የተፈጥሮ ሀብት አርበኛ የሆኑት ሬንጀሮች ማህበር የበለጠ ለማጠናከር እንዲተጉ የቤት ስራ የሚሰጥ ነው ብለዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት የኮፕ32 ብሔራዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ስብሰባ ተካሄደ
Nov 27, 2025 182
አዲስ አበባ፤ ህዳር 18/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት 32ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 32) ብሔራዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ስብሰባ በዛሬው ዕለት ተካሂዷል፡፡ በትናንትናው እለት የኮፕ 32 ተወካይ ፕሬዝደንት መሰየምን ተከትሎ ዛሬ ጠዋት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ቁልፍ የዝግጅት ተግባራትን ለማቀናጀት የሚያስችል የብሔራዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ስብሰባ መደረጉን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። ስብሰባው ኢትዮጵያ ኮፕ 32ን ስታስተናግድ አካታች እና በሚገባ የተሰናዳ ጉባኤ እንድታሳካ ለማረጋገጥ መንግሥት ያለውን ቁርጠኝነት ያሳየበት እንደነበርም ተገልጿል።
ፓርኩ በተደረገለት ጥበቃና እንክብካቤ የዱር እንስሳት ቁጥር እየጨመረ ነው
Nov 26, 2025 227
ገንዳውኃ፣ ሕዳር 17/2018(ኢዜአ)፡ - የጎደቤ ብሔራዊ ፓርክ በተደረገለት የብዝኃ ህይወት ጥበቃና እንክብካቤ የዱር እንስሳቱ ቁጥር እየጨመረ እፅዋቱም እየተስፋፉ መሆኑን የፓርኩ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ይርጋ ታከለ፤ የፓርኩን ደህንነት ለመጠበቅ በመንግስት እየተደረገ ያለውን ጥረት እንዲያግዙ ከሃይማኖት አባቶችና ከሌሎችም የአካባቢው የሕብረተሰብ ክፍሎች ጋር ተደጋጋሚ ውይይትና ምክክር መደረጉን ለኢዜአ ገልጸዋል። በዚህም ሕብረተሰቡ ገንዘብና ቁሳቁስ በማዋጣት ጭምር በፓርኩ ውስጥ የስካውት መጠለያ ካምፕና የንፁህ መጠጥ ውሃ ግንባታ በማከናወን የተጠናከረ ጥበቃ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ተከትሎም በፓርኩ ውሰጥ የሚገኘው የአጥቢ እንስሳት ዝርያ ቁጥር ከ27 ወደ 30 ሲያድግ እፅዋቶች ደግሞ እየተስፋፋ መምጣታቸውን አስረድተዋል። በተጨማሪም በሕገወጥ አደንና ደን ጭፍጨፋ ተሰደው የነበሩ የዱር እንስሳት እንዲመለሱና በመጥፋት ላይ የነበሩ የእፅዋት ዝርያዎች እንደገና እንዲያገግሙ ማስቻሉንም አንስተዋል። ፓርኩ በአብዛኛው የሳር እና ቁጥቋጦ ዝርያ የበዛበት ቢሆንም ትላልቅ የደን ዛፎች ባለቤት እንደሆነም በጥናት መለየቱን አስታውቀዋል። በፓርኩ ከእንስሳት የቆላ አጋዘን፣ ነብር፣ ጅብ፣ ጉሬዛ ያሉ ሲሆን፤ ከአእዋፋት ደግሞ ባለነጭ ጀርባ የአፍሪካ ጆፌ አሞራ፣ ቆቅ፣ ዥግራና ሌሎች የዱር እንስሳት፤ እንዲሁም ከደን እፅዋት " ዞቢ ፣ ዲዛ ፣ ኩመር ፣ ወይባ፣ አባሎ፣ ሰርኪን " እና ሌሎችም በፓርኩ ውስጥ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል። ይሄን የሀገር ትልቅ ሃብት በሰፊው በማስተዋወቅና ጎብኚዎች ወደ አካባቢው እንዲመጡ በማድረግ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግና የአካባቢውን ሕብረተሰብ ተጠቃሚ ለመድረግ ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። ከአካባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ አምሳሉ ደረጀ በሰጡት አስተያየት፤ ከዚህ በፊት በፓርኩ ክልል ውስጥ የቤት እንስሳት ስምሪት፤ ደን ጭፍጨፋና ሕገወጥ አደን በብዛት ይካሄድ እንደነበር አውስተዋል። አሁን ፓርኩን መጠበቅ የጽሕፈት ቤቱ ብቻ ሳይሆን የሁሉም ማህበረሰብ ኃላፊነት መሆኑን ተገንዝበው ድጋፍ በማድረግ ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን ገልጸዋል። ፓርኩ የሀገር ሀብት ነው፤ ይህን ሀብት በመጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ ደግሞ የእኛ ሃላፊነት ነው ያሉት ደግሞ አርሶ አደር ደመቀ ሰማ ናቸው። በፓርኩ ላይ ጉዳት የሚያስከትሉ ግለሰቦች ተይዘው እንዲቀጡ በማድረግ ለፓርኩ ደሕንነት መጠበቅ የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ተናግረዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን ምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ እና በመተማ ወረዳ መካከል የሚገኘው የጎደቤ ብሄራዊ ፓርክ በጥብቅ ደንነት ከቆየ በኋላ በአማራ ክልል ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 152/2009 ዓ.ም ፓርክ ሆኖ የተቋቋመና 18ሺህ 691 ሄክታር ስፋት ያለው መሆኑ ተጠቁሟል። ፓርኩ ከባሕርዳር በ411 ኪሎ ሜትር፣ ከጎንደር ደግሞ በ237ኪሎ ሜትር እንዲሁም ከዞኑ ማዕከል ገንዳውሃ ከተማ ደግሞ በ133 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ እንደሚገኝ ተመልክቷል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) የኮፕ 32 ተወካይ ፕሬዝደንት በመሆን ተመደቡ
Nov 26, 2025 149
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 17/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)ን የኮፕ 32 ተወካይ ፕሬዝደንት አድርጎ መድቧል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጸህፈት ቤት እንዳስታወቀው፤ በተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ማእቀፍ ኮንቬንሽን መሠረት ኢትዮጵያ የኮፕ 32 አስተናጋጅ ሀገር መሆኗን ተከትሎ የኢትዮጵያ መንግሥት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑትን ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)ን የኮፕ 32 ተወካይ ፕሬዝደንት አድርጎ መድቧል። ዶክተር ጌዲዮን ከሀገር ውስጥ የሥራ ኃላፊዎች፣ ከተባበሩት መንግሥታት አካላት እና አለም አቀፍ አጋሮች ጋር በመተባበር የኮፕ 32 ዝግጅትን እንደሚመሩም አስታውቋል። የኢትዮጵያ መንግሥት የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ማእቀፍ ኮንቬንሽን አባል ሀገራት ለኢትዮጵያ የማዘጋጀት ኃላፊነት በመስጠታቸው ምስጋናውን አቅርቧል፡፡ በዶክተር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ አስተባባሪነት ከአለም የአየር ንብረት ጥበቃ ማኅበረሰብ ጋር በቅርበት ለመሥራት ዝግጁ መሆኑንም ገልጿል፡፡
ዝቅተኛ በካይ ጋዝ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ርብርብ እየተደረገ ነው
Nov 24, 2025 294
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 15/2018 (ኢዜአ)፡- በትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ዘርፍ ዝቅተኛ በካይ ጋዝ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስቴሩ ከፓወር አፍሪካ ጋር በመተባበር የሚያዘጋጀው ሁለተኛው ኢትዮ ግሪን ሞቢሊቲ 2025 ኤግዚቢሽንና ባዛር ከታኅሣሥ 9 እስከ 12 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ያካሂዳል፡፡ ሚኒስትሩ አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ሁለተኛውን ኢትዮ ግሪን ሞቢሊቲ 2025 ኤግዚቢሽንና ባዛር ለማካሄድ በተደረጉ ዝግጅቶችና በሚጠበቁ ውጤቶች ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል። ሚኒስትር አለሙ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት መተግበር የጀመረው አረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ መደላድል እየፈጠረ ነው። የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ ሥራዎች ኢትዮጵያ ኮፕ 32 የዓለም አየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ እንድታስተናግድ እንድትመረጥ አድርጓታል ሲሉም ጠቅሰዋል። በትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ዘርፍም ታዳሽ ኃይልም ሆነ ዝቅተኛ በካይ ጋዝ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎች በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ከታኅሣሥ 9 እስከ 12 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ የሚካሄደው ኢትዮ ግሪን ሞቢሊቲ ኤግዚብሽንና ባዛር ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ አዎንታዊ ሚና እንደሚጫወትም ተናግረዋል። በኤግዚቢሽን እና ባዛሩ ላይ ኤሌክትሪክን ጨምሮ የተለያዩ ታዳሽ ኃይል የሚጠቀሙ ተሽከርካሪ አምራቾች፣ ቴክኖሎጂ አቅራቢዎች፣ በዘርፉ የተሰማሩ ዓለም አቀፍ ተቋማት እና የጥናትና ምርምር ተቋማት እንደሚሳተፉ አብራርተዋል። በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችና መፍትሔ አቅጣጫዎች ላይ በጋራ ውይይት የሚደረግበት መርሐ ግብር መሰናዳቱንም አመልክተዋል።
በገጠር ክላስተሮች እየተከናወነ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ ነው
Nov 22, 2025 288
ድሬዳዋ፤ ሕዳር 13/2018(ኢዜአ) ፡- በድሬዳዋ የገጠር ክላስተሮች እየተከናወነ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ለስነ ምህዳር ጥበቃና ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ መሆኑን የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ባለሙያ አቶ ገረመው ረጋሳ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በድሬዳዋ የገጠር ክላስተሮች የአፈርና የውሃ ጥበቃ ስራ በስፋት በመከናወን ላይ መሆኑንና በዚህም ውጤት እየመጣ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በድሬዳዋ የገጠር ክላስተሮች እየተከናወነ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ለስነ ምህዳር ጥበቃና ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ ስለመሆኑ አንስተዋል። በዘመቻ እና በመደበኛ መርሃ ግብር በተራቆቱ ተፋሰሶች ላይ በተከናወኑ የልማት ስራዎች ከ60 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ማልማት መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመጠበቅም ባለፈ ምርታማነትን ማሳደግ ማስቻሉን ገልጸዋል። በቢሮው የህብረት ስራ ማስፋፊያ፣ ግብይትና ግብአት ኤጀንሲ ባለሙያ አቶ ያሲን ኢብራሂም፤ የተፋሰስ ልማት ስራ የአካባቢ ስነ ምህዳርን በመጠበቅ ረገድ የሚታይ ውጤት የመጣበት መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም በገጠር አካባቢዎች ምርታማነትን በማሳደግ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ያስቻለ መሆኑንም አንስተዋል። በድሬዳዋ የገጠር ክላስተሮች ወጣቶችና ሴቶች ተደራጅተው በሌማት ትሩፋት ኢንሸቲቮች ላይ በመሳተፍ ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። የለገ ዶል ገጠር ቀበሌ አርሶ አደር ኢብሳ ሙሳ እና አርሶ አደር አህመድ ዳዌ፤ በአካባቢው የተከናወነው የልማት ስራ በብዙ መልኩ የጠቀማቸውና ውጤትም ያገኙበት መሆኑን ተናግረዋል። የቀበሌው የግብርና ባለሙያ አቶ ምህረት መታዬት፤ አርሶ አደሮቹ በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም በእንስሳት እርባታ በመሰማራት ስኬታማ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤን እንድታስተናግድ መመረጧ ሀገሪቷ ለአየር ንብረት ለውጥ ፖሊሲና ስትራቴጂ ትግበራ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር ያረጋገጠ ነው
Nov 21, 2025 332
አዲስ አበባ፤ሕዳር 12/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት (COP-32) ጉባኤን እንድታስተናግድ መመረጧ ሀገሪቷ ለአየር ንብረት ለውጥ ፖሊሲና ስትራቴጂ ትግበራ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር ያረጋገጠ ነው ሲሉ የአረንጓዴ አሻራ ሀገራዊ መርሃ-ግብር የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ገለፁ። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬቶችም ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት ጉልህ ድርሻ እየተወጣ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአካባቢ ስነ-ምኅዳር ደኅንነት በማስጠበቅ ጉልህ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ኢትዮጵያ በብራዚል ቤለም በተካሄደው የዓለም የአየር ንብረት (COP-30) ጉባኤ ላይ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት (COP-32) ጉባኤ ለማስተናገድ መመረጧ ይታወቃል። አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉትም፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እስካሁን ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን በመትከል ዓለም አቀፍ ዕውቅናን ያስገኘ አስደማሚ የልማት ስኬት ተመዝግቧል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬትም 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (COP-32) ለማስተናገድ ተመራጭ እንድትሆን ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ገልጸዋል። ጉባኤው ላይ የበርካታ ሀገራት መሪዎች፣ የዓለም አቀፍ ተቋማት የስራ ኃላፊዎች ምክክር በማድረግ ውሳኔ የሚያሳልፉበት መድረክ በመሆኑ ልምድና ተሞክሮን ለመጋራት ትልቅ ትርጉም እንደሚሰጠው ተናግረዋል። የአየር ንብረት ጉባኤን ለማስተናገድ ጥያቄ የሚያቀርቡ ሀገራት በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሥርዓት የሚያከናወኑት የመሠረተ ልማት ግንባታ ስራና ያስመዘገቡት ስኬት እንደሚታይ አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ ተከላና የአየር ንብረት ፖሊሲና ስትራቴጂ ትግበራ ያላት ቁርጠኝነት ጉባኤውን ለማስተናገድ ያቀረበችው ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ እንዲያገኝ ማድረጉን አንስተዋል። በኢትዮጵያ የተካሄደው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤና ሌሎች ዓለም አቀፍ መድረኮችን በብቃት የማስተናገድ ልምድና አቅም ለመመረጧ ሌላኛው ዐብይ ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። የፓሪሱን ስምምነት ለመተግበር በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ፖሊሲና ስትራቴጂዎች ታሳቢ ያደረጉ የኢትዮጵያ የልማት ተነሳሽነቶችም በዓለም አቀፍ ደረጃ በአርዓያነት የሚወሰዱ መሆናቸውን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬቶችም ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የራሱን ድርሻ እየተወጣ እንደሚገኝም ተናግረዋል። አረንጓዴ አሻራ የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በመጠበቅ፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥና የሥራ ዕድል ፈጠራን በመደገፍ ሂደት የኢኮኖሚ ዕድገትን በማስቀጠል ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም ገልጸዋል። ለአየር ንብረት ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታም በ2050 ከካርቦን ልቀት ነፃ የኢኮኖሚ ሥርዓት ለመገንባት የተያዘውን ግብ ዕውን ለማድረግ ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል።