አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው በጋ የሆኑ አካባቢዎች መደበኛ እና ከመደበኛ በታች የዝናብ ስርጭት ይኖራቸዋል
Sep 18, 2025 102
አዳማ ፤ መስከረም 8/2018(ኢዜአ)፦- ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው በጋ የሆኑ አካባቢዎች መደበኛ እና ከመደበኛ በታች የዝናብ ስርጭት እንደሚኖራቸው የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ የክረምት ወቅት የአየር ጸባይ ትንበያ ግምገማና የበጋ ወቅት የአየር ሁኔታ ጸባይ አዝማሚያ ትንበያ ይፋ ለማድረግ ያዘጋጀው መድረክ በአዳማ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ ላይ የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ እንዳስታወቁት ኢንስቲትዩቱ የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ የአየር ትንበያ መረጃዎችን በወቅቱ ለተጠቃሚዎች እየሰጠ ይገኛል። ትንበያዎቹ ለግብርና፣ ለውሀ ሀብት አስተዳደር፣ ለአደጋ ስጋት ዝግጅት፣ ለጤናና ለአካባቢ ጥበቃ ስራዎች እያገለገሉ መሆናቸውን ገልፀዋል። የትንበያዎቹን ትክክለኛነት ለማሳደግም ሳይንሳዊ ዘዴን በመጠቀም መሰራታቸውን ጠቁመው ይህም የኢንስቲትዩቱን በ2017/18 የክረምት ወቅት የአየር ጸባይ ትንበያ ውጤታማ እንዳደረገው ገልጸዋል። አሁን ላይ ኢኒስቲትዩቱ የበጋ ወቅት ትንበያ መረጃዎችን ለህብረተሰቡና ለተቋማት ይፋ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው በጋ በሆኑት የቦረናና ጉጂ ዞኖች፣ ሲዳማና ደቡብ ኢትዮጵያ መደበኛ ዝናብ እንደሚኖራቸው ዋና ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል። እንዲሁም የሶማሌ ክልል ደቡባዊ ክፍል ደግሞ ከመደበኛ በታች የሆነ የዝናብ መጠንና ስርጭት እንደሚያገኙ አክለዋል። በሌላ በኩል የምእራብና ደቡብ ምእራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚያገኙ አቶ ፈጠነ ተናግረዋል። ህብረተሰቡ እነዚህን መረጃዎች በመጠቀም የአደጋ ተጋላጭነትን በመቀነስ ስጋቶችን ወደ መልካም አጋጣሚዎች በመቀየር ምርትና ምርታማነቱን እንዲያሳድግ አስገንዝበዋል። የውሀና ኢነርጂ ሚኒስትር (ዶ/ር) ኢ/ር ሀብታሙ ኢተፋ በበኩላቸው ኢንስቲትዩቱ መረጃን በማዘመን እየሰጠ ያለው ትንበያ ለተለያዩ ተቋማት ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልፀዋል። በተለይ ሴክተር ተኮር መረጃን በወቅቱ ለተጠቃሚዎች በመስጠት የሚደርሰውን ጉዳት ለመቀነስና ምርታማነትን ለማሳደግ ከፍተኛ አበርክቶ እንዳለው ገልፀዋል። በተለይ በውሀ ሴክተሩ የሚቀርቡ መረጃዎችን ሚኒስቴሩ በአግባቡ በመጠቀም የታላቁ የኢትዮጵያ ግድብ የውሀ ሙሌትን በተሳካ ሁኔታ ማከናወኑን ለአብነት ጠቅሰዋል። በመሆኑም የሚሰጡትን ትንበያዎች በአግባቡ በመተንተንና ተግባር ላይ ለማዋል ሁሉም ሴክተር መስሪያ ቤቶች እንዲጠቀሙበት ምክረ ሀሳብ አቅርበዋል። በመድረኩ ላይ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሁሉም ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዎችና ምክትል ሰብሳቢዎች፣ የፌዴራል ተቋማት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ ባለድርሻ አካላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እየተሳተፉ ናቸው።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ስትራቴጂዎችን ወደ ተግባር በመቀየር እያከናወነች ያለው ስራ የሚደነቅ ነው -የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከፍተኛ የአየር ነብረት አስተዳደር ባለሙያ
Sep 18, 2025 95
አዲስ አበባ፤ መስከረም 8/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ስትራቴጂዎችን ወደ ተግባራዊ እውነታ በመቀየር እያከናወነች ያለው ስራ የሚደነቅ ነው ሲሉ የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከፍተኛ የአየር ነብረት አስተዳደር ባለሙያ ጀምስ ሙሮምቤድዚ ገለጹ። የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ኢሴኤ) ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እያከናወነች ላለው ስራ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ዩኤንኢሴኤ) ከፍተኛ የአየር ነብረት አስተዳደር ባለሙያ ጀምስ ሙሮምቤድዚ የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተጽእኖዎችን ለመከላከል አፍሪካ በቀል መፍትሄዎችን የመጠቀም ባህል ሊያድግ እንደሚገባ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ገልጸዋል። በዚህ ረገድም አረንጓዴ አሻራ በመላው አፍሪካ በስፋት ሊተገበር የሚገባ ኢኒሼቲቭ ነው ሲሉ አድናቆታቸውን ገልጸዋል። የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ለንጹህ ኢነርጂ ምንጭነት እና ለዘላቂ የኢንዱስትሪ እድገት ከፍተኛ ሚና እንደሚወጣ አመልክተዋል። ኢትዮጵያ የካርቦን ልህቀትን በመቀነስ በዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች እንደምትገኝ መስክረዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ እድገት ስትራቴጂ ከስነ ምህዳር ማገገም፣ የህዳሴ ግድብ ግንባታ፣ የካርቦት ልህቀት ቅነሳ እና የኤሌክትሪክ መኪኖች አገልግሎት እርምጃዎች ጋር ተዳምሮ ለአረንጓዴ እና ታዳሽ ኃይል ልማት አስተዋጽኦ እንደሚያደርግም ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ስትራቴጂዎችን ወደ ተግባራዊ እውነታ በመቀየር እያከናወነች ያለው ስራ የሚደነቅ ነው ብለዋል። የአፍሪካ መዲና የሆነችው ኢትዮጵያ በአህጉሪቷ ውስጥ ያላት ስትራቴጂካዊ ስፍራ ከሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጋር በመተባበር የአየር ንብርተ መፍትሄዎችን ለመተግበር ምቹ አጋጣሚ እንደሚፈጥርላትም ነው የገለጹት ከፍተኛ ባለሙያው። የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ መሆኗም የአህጉሪቷ የአየር ንብረት ፖሊሲ እና ስትራቴጂ ማዕከል እንደሚያደርጋት ተናግረዋል። ባለሙያው ኢትዮጵያ እና ኢሴኤ ለረጅም ጊዜ የቆየ አጋርነት እንዳላቸው ገልጸው በአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ እና አቅም ግንባታ የነቃ ተሳትፎ እያደረገ እንደሚገኝ አመልክተዋል። ኢሲኤ ከኢትዮጵያ ተቋማት ጋር በመሆን ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም ግንባታን እየደገፈ መሆኑን ተናግረዋል። የአየር ሁኔታ ትንበያ እና ቅኝት ስርዓትን ማጠናከር እንዲሁም የአረንጓዴ አሻራ በፖሊሲ እና በትግበራ ደረጃ የመደገፍ ስራ መኖሩንም ጠቅሰዋል።
በአረንጓዴ አሻራ የተተከለውን ችግኝ የመንከባከብ ተግባር ተጠናክሮ ቀጥሏል
Sep 13, 2025 380
ባሕርዳር፤ መስከረም 3/2018 (ኢዜአ) ፡- በአማራ ክልል በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከለውን ችግኝ ለውጤት ለማብቃት የመንከባከቡ ተግባር ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር እስመለዓለም ምህረት፤ በክረምቱ የተተከለውን ችግኝ የፅድቀት ምጣኔ 85 በመቶ ለማድረስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ለኢዜአ ተናግረዋል። ለዚህም ሕብረተሰቡ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በየአካባቢው የተከለውን ችግኝ ለውጤት ለማብቃት የመንከባከብ ተግባር ማጠናከሩን ገልጸዋል። ሕብረተሰቡ የችግኝን ጠቀሜታ በየጊዜው በውል እየተረዳ መምጣቱን ገልጸው ከ205 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የተተከለው ችግኝ ከነሐሴ 2017 ዓ.ም መጨረሻ ጀምሮ የአረምና የመንከባከብ ተግባር በንቃት እየተከናወነ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ከእንክብካቤው ጎን ለጎንም በጠፋ ችግኝ የመተካት ተግባርም ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ እንደሚገኝም አንስተዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከለው ችግኝ የክልሉን የደን ሽፋን በአንድ በመቶ በማሳደግ ወደ 17 ነጥብ 3 በመቶ እንደሚያደርሰው ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የሰከላ ወረዳ አርሶ አደር አለሙ ወልዴ በሰጡት አስተያየት፤ በክረምት ወቅት በግልና በወል መሬት የተከሉትን ችግኝ በማረም እየተንከባከቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የችግኝን ጥቅም በአግባቡ እየተረዳን በመምጣታችን የእንክብካቤ ተግባሩን እያከናወንን ያለነው በራሳችን ተነሳሽነትና ፍላጎት ነው ብለዋል። በአረንጓዴ አሻራ የተከልነው ችግኝ የአፈር መሸርሸር እንዲቀንስ አግዟል ያሉት ደግሞ በደቡብ ጎንደር ዞን የፋርጣ ወረዳ አርሶ አደር ተስፋሁን መንጌ ናቸው። በሰሜን ጎጃም ዞን የአዴት ወረዳ አርሶ አደር ምህረቱ አስማረ፤ ከቤተሰቦቻቸው ጋር በመሆን የተከሉትን ችግኝ ተንከባክበው እያሳደጉ መሆኑን ተናግረዋል። ከግብርና ቢሮው የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፤ ቀደም ባለው ዓመት የክረምት ወቅት በአማራ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከለው ችግኝ በተደረገለት እንክብካቤ 82 በመቶውን ማፅደቅ ተችሏል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም እያደረገች ያለው ጥረት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው
Sep 13, 2025 381
ጂንካ፤ መስከረም 3/2018 (ኢዜአ)ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋም ለድርቅ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እያደረገች ያለው ጥረት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ በኢጋድ የክፍለ-አህጉሩ ዳይሬክተር ሙባረክ ማቦያ ገለፁ። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) አባል አገራት ተወካዮች በኢጋድ መሪነት በኢትዮጵያ ለድርቅ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች እየተተገበሩ ያሉ ፕሮጀክቶች አፈፃፀምን ተመልክተዋል። ልዑካኑ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደቡብ ኦሞ ዞን በና-ፀማይ ወረዳ ድርቅን ለመቋቋም በሚደረገው ሂደት በአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ ዘንድ የመጡ ተጨባጭ ለውጦችንም መመልከት ችለዋል። በኢጋድ የክፍለ አህጉሩ ዳይሬክተር ሙባረክ ማቦያ እንደገለፁት፤ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋም ለድርቅ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እያደረገች ያለው ጥረት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው። በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና እንክብካቤ፣ ዝናብ አጠር በሆኑ አካባቢዎች በመስኖ ልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ጥረቶች ውጤት እያስመዘገቡ እንደሆነ መመልከታቸውን ተናግረዋል። እንዲሁም የአርብቶ አደሩን የኢኮኖሚ አቅም ለማሳደግ፣ የእንስሳት ምርታማነትን ለማሻሻል፣ የንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ሽፋንን ለማሳደግና ድርቅን የሚቋቋም ማህበረሰብ ለመፍጠር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የሚበረታቱ ናቸው ብለዋል። በሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን በዝርዝር አቅርበው እንደነበር ያስታወሱት ዳይሬክተሩ በኢትዮጵያ ያደረግነው ምልከታም ይህንኑ በተግባር የሚያሳይ ነው ብለዋል። በግብርና ሚኒስቴር የኢትዮጵያ የድርቅ መቋቋም እና የአርብቶ አደር ኑሮ ማሻሻያ ፕሮግራም ብሔራዊ አስተባባሪ ጀማል አልዬ፤ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋም የተሻለ ውጤት ማምጣቷን ገልጸዋል። የኢጋድ አባል አገራት በኢትዮጵያ እያደረጉ ያሉት ጉብኝትም ያለውን ልምድና ተሞክሮ ለመቅሰምና በሌሎች የድርጅቱ አባል ሀገራትም ተሞክሮውን ለማስፋት ታስቦ የተደረገ እንደሆነም አስረድተዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር በበኩላቸው፤ በክልሉ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የአርብቶ አደሩን ኑሮ ለማሻሻል እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጨባጭ ለውጥ እያመጡ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይም የእንስሳት ጤናን በመጠበቅ፣ ድርቅን አስቀድሞ በመከላከል፣ አርብቶ አደሩን ከዝናብ ጥገኝነት በማላቀቅ ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖ የማይበገር ኢኮኖሚን ለመገንባት የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመስኖና ቆላማ አካባቢ ልማት ቢሮ የአደጋ ስጋት ቅነሳና አካታች የኢኮኖሚ እሴት ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ ስዩም መታፈሪያ (ዶ/ር) ባደረጉት ገለፃ የደቡብ ኦሞ ዞን ዝናብ አጠርና በተደጋጋሚ ለድርቅ ተጋላጭ የሆነ አካባቢ እንደነበር ገልጸው ተጋላጭነቱን ለመቀነስ በተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ ተግባራት ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን ገልፀዋል። ቡድኑ በደቡብ ኦሞ ዞን በና ፀማይ ወረዳ ለመስኖ፣ ለሰውና ለእንስሳት ሁለገብ አገልግሎት የሚሰጠውና 300 ሜትር ጥልቀት ያለው እንዲሁም በፀሐይ ኃይል በሰከንድ 26 ሊትር ውሃ የሚያመነጨውን ጥልቅ የውሃ ጉድጓድ ፕሮጀክትንም ተመልክቷል። ከዚህ በተጨማሪ የእንስሳት ማቆያ እና የእንስሳት የገበያ ማዕከል፣ የከብቶች የመኖ ልማት እና የመኖ ማከማቻ መጋዘንና ሌሎች ፕሮጀክቶችንም ጎብኝተዋል። ልዑካን ቡድኑ በአፋርና በሶማሌ ክልል ምልከታ ያደረጉ ሲሆን ከደቡብ ኢትዮጵያ በመቀጠል ወደ ኦሮሚያ ክልል በማቅናት በቦረና ዞን ምልከታ እንደሚያደርጉም ተመላክቷል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የጀመረቻቸውን ኢንሼቲቮች በደቡብ ደቡብ ትብብር ማጠናከር ይገባል
Sep 12, 2025 407
አዲስ አበባ፤ መስከረም 2/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የጀመረቻቸውን ኢንሼቲቮች በደቡብ ደቡብ ትብብር ማጠናከር እንደሚገባ የዓለም አቀፍ ተቋማት መሪዎች ገለጹ፡፡ የአፍሪካ የበካይ ጋዝ ልቀት መጠን ከአራት በመቶ ባይበልጥም በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ከፍተኛ ተጎጂ መሆኗ አልቀረም፡፡ በተለይም አፍሪካን ጨምሮ በማደግ ላይ ያሉ ሀገራት በአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ የሚደርስባቸውን ችግር የህልውና ጥያቄ ውስጥ የሚገባ ሆኗል፡፡ አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የጎላ በካይ ጋዝ ከሚለቁ ሀገራት ከመጠበቅ የራሷን መፍትሔ መፈለግ አለባት የሚለው የብዙ ዓለም አቀፍ ተቋማት ምክረ ሀሳብ ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር እንደ ቻይና እና ጃፓን በቴክኖሎጂ ከበለጸጉ ሀገራት ጋር በደቡብ ደቡብ ትብብር የቴክኖሎጂ አቅምን ማሳደግ እንደሚገባም ይገልፃሉ፡፡ የዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት ረዳት ዋና ጸሀፊ ቶማስ አሳሬ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የአየር ንብረት ፋይናንስ በማመንጨት እና ጎረቤት ሀገራት በታዳሽ ኃይል በማስተሳሰር የጎላ አበርክቶ አለው፡፡ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በቢሊዬን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ እየገነባች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአመራር ቁርጠኝነት እና የኢትዮጵያ ህዝብ ተሳትፎ የላቀ አበርክቶ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት በደቡብ ደቡብ ትብብር ማጠናከር ይገባል ብለዋል፡፡ የዓለም የእርሻና ምግብ ድርጅት ረዳት ዳይሬክተር ጀነራል እና የአፍሪካ ተጠሪ አበበ ኃይለገብርኤል (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስን ከፍተኛ በካይ ጋዝ የሚለቁት ያደጉ ሀገራት እንዲሸፍኑ የወጡ የፓሪስ እና ሌሎች ዓለም አቀፍ ስምምነቶች በአግባቡ ገቢራዊ አልተደረጉም ብለዋል፡፡ የአፍሪካ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የደቡብ ደቡብ ትብብርን በማጠናከር የቴክኖሎጂ አቅማቸውን ማሳደግ እንዳለባቸውም ገልጸዋል፡፡ አፍሪካ የታዳሽ ሀይል፣ እምቅ የማዕድንና ሌሎች የተፈጥሮ ጸጋዎች ያሏት አህጉር መሆኗን በመጥቀስ፤ በደቡብ ደቡብ ትብብር ጸጋዋን የምትጠቀምበት ቴክኖሎጂ ማላመድ አለባት ብለዋል፡፡ በደቡብ ደቡብ ትብብር ማዕቀፍ እንደ ቻይና ያሉ ሀገራት በብዙ ተፈትነው መሰረት የያዘ የቴክኖሎጂ አቅም ገንብተዋል ያሉት ዶክተር አበበ ፤ አፍሪካ ዘግይታ መግባቷን /late comer advantage/ እንደ እድል መጠቀም እንዳለባት ገልጸዋል፡፡
ጉባኤው አፍሪካ ለዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ የመፍትሔ ማዕከል መሆኗን በግልጽ ያሳየ ነው - ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ
Sep 10, 2025 466
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2017(ኢዜአ)፦ ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ አፍሪካ የመፍትሔና የታዳሽ ኃይል ማዕከል መሆኗን ያሳየችበት መሆኑን የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ገለጹ፡፡ "ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፣ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ ለሶስት ቀናት ሲካሄድ የነበረው ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ዛሬ ተጠናቋል፡፡ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በመዝጊያ መርሃ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ አፍሪካ ግልጽ አቋሟን ያንጸባረቀችበት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ ተጎጂ ብቻ ሳይሆን በአረንጓዴ ልማትና በታዳሽ ሀይል ዓለም አቀፍ የመፍትሔ ማዕከል መሆኗን አሳይቷል ብለዋል፡፡ ዓላማችን የበለጸገች፣ አይበገሬና አረንጓዴ አፍሪካን መፍጠር ነው ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ የኤሌክትሪክ ሃይል የማያገኙ 600 ሚሊዮን አፍሪካውያን መኖራቸው ኢፍትሐዊነት መሆኑን የዓለም ማህበረሰብ ሊገነዘብ እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን የመቋቋም ተግባራችን ያለንን ሰፊ ሀብት፣ የታዳሽ ሃይል ልማትና የአየር ንብረት ለውጥ ፍትህ ላይ ማተኮር አለበት ብለዋል፡፡ በአፍሪካ ያለውን እምቅ የውሃና የጸሀይ ሀይል በመጠቀም ሁሉም ዜጎችና ድርጅቶች የኤሌክትሪክ ሃይል እንዲያገኙ ማድረግ እና በሚሊዮን ለሚቆጠሩ ወጣቶች የስራ እድል መፍጠር እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ አፍሪካውያን በዓለም እንደ ተረጂ የምንታይበትን ትርክት በተባበረ አቅማችን መቀየርና የዓለም የመፍትሔ አካል መሆናችንን ማሳየት ይኖርብናል ብለዋል፡፡ አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ ጉዳይ ለዓለም የሚተርፍ መፍትሔ አላት ያሉት ፕሬዝዳንቱ ቢሊዮን ችግኞች በየዓመቱ የሚተከሉበት የአረንጓዴ ዐሻራ፣ የታዳሽ ኃይል ልማት፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃን በምሳሌነት ጠቅሰዋል። የአዲስ አበባ የመሪዎች ቃል ኪዳን መጽደቅ ትልቅ እርምጃ ነው ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ በራሷ አቅም መፍትሔ እንደምታመጣ የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የመሪዎች ቃል ኪዳን የታዳሽ ኃይልና የአረንጓዴ ልማትን በማስፋት ነገን መገንባት፣ ወሳኝ ማዕድናትን ጨምሮ የአህጉሪቱን የተፈጥሮ ሀብት በራስ ማስተዳደርና መጠቀም፣ ጥብቅ ደኖችን ጨምሮ የተፈጥሮ ቅርሶቻችንን መጠበቅ ላይ ያተኮሩ ሦስት ምሰሶዎች እንዳሉት አስረድተዋል። የአዲስ አበባ የመሪዎች ቃል ኪዳን በአጭር ጊዜ ዕቅድ ወጥቶለት ሊተገበር የሚገባ መሆኑንም አስገንዝበዋል።
ኢትዮጵያ ሁለተኛውን ለአየር ንብረት ተስማሚ የሆነ ገበያ ተኮር የግብርና ፕሮግራም ይፋ አደረገች
Sep 10, 2025 196
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 5/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ሁለተኛውን ምዕራፍ ለአየር ንብረት ተስማሚ የሆነ ገበያ ተኮር የኮታ ገጠም የግብርና ፕሮግራምን ይፋ አድርጋለች። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ(ዶ/ር)፥ መንግስት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ሥራ ቅድሚያ በመስጠት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ግብርና የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ትልቁ አንቀሳቃሽ መሆኑን ገልጸው በወጪ ንግድ እና የሀገር ውስጥ የምግብ ፍጆታን በማሟላት ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የመጀመሪያው ምዕራፍ ገበያ ተኮር የግብርና ፕሮግራም ትግበራ ከ4 ነጥብ 4 ሚሊዮን በላይ አርሶ አደሮችን ተጠቃሚ እንዳደረገና በጥራጥሬ፣ አትክልትና ፍራፍሬ ዘርፍ አመርቂ ውጤት እንደተመዘገበበት ተናግረዋል። ሁለተኛው ምዕራፍ የተገኙ ስኬቶችን ማስቀጠል በሚቻልበት መንገድ መዘጋጀቱን አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሤ(ዶ/ር) ፕሮግራሙ በርካታ ግቦች እንዳሉት ጠቅሰዋል። ፕሮግራሙ ኢትዮጵያ አነስተኛ የእርሻ ማሳ ያላቸው አርሶ አደሮች በኩታ ገጠም እርሻ ተጠቃሚ የሚያደርግ ለአየር ንብረት ተስማሚ የሆነ ገበያ ተኮር ግብርናን ለማሳደግ ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል። ፕሮግራሙ ግብርና የምግብ ዋስትና እና የኢኮኖሚ ለውጥ አንቀሳቃሽ የመሆን አቅሙን ለማጎልበት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ጨምረዋል። በዴንማርክ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የልማት ፖሊሲ ምክትል ጸሐፊ ኦሌ ቶንኬ የዴንማርክ መንግስት ለኢትዮጵያ የግብርና ዘርፍ የ75 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማድረጉን ገልጸዋል። ዴንማርክ ለኢኮኖሚ እድገት እና ለሥራ ፈጠራ አስፈላጊ በሆነው የግብርና ዘርፍ ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር በመስራቷና የልማት አጋር በመሆኗ ኩራት እንደሚሰማትም ተናግረዋል።
ሦስተኛው በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ዕቅድ የአረንጓዴ ልማት ግቦችን የሚያሳካ ነው
Sep 10, 2025 260
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 5/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሦስተኛው በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ብሔራዊ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ የ10 ዓመት ዕቅድ የአረንጓዴ ልማት ግቦችን የሚያሳካ መሆኑን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ፡፡ ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ የሦስተኛ ቀን ውሎ የውይይት መድረክ ዛሬም በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ተካሂዷል። የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ በግብርና፣ የአፈር ማዳበሪያ፣ ታዳሽ ሀይል፣ የአየር ንብረት ፋይናንስ እና ሌሎች ጉዳዮች ላይ በጋራ መስራት የሚያስችሉ ውይይቶች ተደርገዋል፡፡ የፕላንና ልማት ሚኒስቴር በዛሬው ዕለት የበካይ ጋዝ ልቀትን በመቀነስ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም ሶስተኛውን በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ የ10 ዓመት ዕቅድ ይፋ አድርጓል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ዕቅዱን ይፋ ባደረጉበት ወቅት፤ በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ዕቅድ በፓሪስ ስምምነት መሰረት በየአምስት ዓመቱ ማሻሻያ እንደሚደረግበት አውስተዋል። ኢትዮጵያም እ.አ.አ ከ2025 እስከ 2035 የሚተገበር ሦስተኛውን በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ብሔራዊ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ዕቅድ ማውጣቷን ገልጸዋል። ዕቅዱ ከኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር፣ ከሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ፣ ከ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ እና ከረጅም ጊዜ የካርበን ልቀት ስትራቴጂክ ዕቅድ ጋር የተጣጣመ መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አማካይነት የደን ሽፋን ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ማለቱን ገልጸው፤ በ2030 ወደ 30 በመቶ ለማሳደግ ታቅዷል ብለዋል። የአስር ዓመቱ ዕቅድ የግብርና ምርታማነትን፣ የከተማ መሰረተ ልማትን፣ የታዳሽ ኃይል አቅርቦትን እና የሰብል ምርታማነትን ተጨባጭ በሆነ መንገድ የሚያሳድግ ነው ብለዋል። በዶሮ እርባታ፣ በንብ ማነብ፣ በስጋ ምርት እንዲሁም በመስኖ ልማትና በሌሎች የግብርና ዘርፎች የተመዘገቡ ለውጦችን ማስቀጠል እንደሚችልም አመልክተዋል። ኢትዮጵያ ለብዝኃ ህይወትና ሥርዓተ ምህዳር ጥበቃ፣ የመሬት መሸርሸርን ለመከላከል ጠንካራና ዘላቂነት ያለው ኢኮኖሚ ለመገንባት በጀት መድባ እየሰራች ነው ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ይጠይቃል ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፣ ብሔራዊ ዕቅዱን ለማሳካት 98 ነጥብ 35 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ለዕቅዱ መሳካት ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ በፋይናንስ፣ በቴክኒክ እና በቴክኖሎጂ ዕገዛ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል። በዓለም ባንክ የምሥራቅ አፍሪካ የአካባቢ ዘርፍ ማናጀር ፖል ማርቲን፤ ባንኩ በኢትዮጵያ ለዘላቂ ደን እና መሬት ልማት አስተዳደር ቅድሚያ በመስጠት በትብበር መስራቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህም የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን መቋቋም የሚያስችል የአፈርና ውሀ ጥበቃ እንዲሁም የተራቆተ መሬት ማገገም ላይ ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል፡፡ የዓለም ሪሶርስ ኢንስቲትዩት ግሎባል ዳይሬክተር ሜላኒ ሮብሰን የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ፣ የኤሌክትሪክ ትራንስፖርት ስርዓትና ሌሎችም ኢኒሼቲቮች የአረንጓዴ ልማትን የሚደግፉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን በራሷ አቅም መቋቋም የሚያስችል እምቅ አቅም እንዳላት ያነሱትን ሀሳብ የኢትዮጵያ ኢኒሼቲቮች አረጋግጠዋል ነው ያሉት። የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ አጋርነት ዓለም አቀፍ ዳይሬክተር ፓብሎ ቬራ (ዶ/ር) በበኩላቸው ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት አድንቀዋል፡፡ ኢትዮጵያ በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ዕቅድ ትግበራ ያስመዘገበችው ስኬት በቀጣናውና በዓለም መሪ ያደርጋታል ብለዋል፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም የኢትዮጵያን ድንቅ ሥራዎች በሌሎችም ሀገራት መድገም እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ ሦስተኛውን በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ብሔራዊ የአየር ንብረት ለውጥ ዕቅድ እንድታሳካ ዓለም አቀፍ የልማት አጋሮች ድጋፍ ሊያደርጉ እንደሚገባ ተናግረዋል።
ለአየር ንብረት ተስማሚ አረንጓዴ ትራንስፖርትን ለማስፋፋት የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Sep 10, 2025 152
አዲስ አበባ ፤ ጳጉሜን 5/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ዘመናዊና ለአየር ንብረት ተስማሚ አረንጓዴ ትራንስፖርትን ለማስፋፋት የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር)ገለጹ። የኢትዮጵያ የምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ከ'ኮይፓ ኢታሊያ' ከተሰኘ ዓለም አቀፍ ድርጅት ጋር ስትራቴጂክ ስምምነት አድርገዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ(ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ የባቡር መሰረተ ልማቶች ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚያዊ ሽግግር ማዕከል ናቸው። መሰረተ ልማቶቹ ወጪን ይቀንሳሉ፣ የገበያ ትስስር ይፈጥራሉ፣ የስራ እድል ያስፋፋሉ፣ አረንጓዴ የኢኮኖሚ ልማትን ይደግፋሉ ብለዋል። ዛሬ የተደረገው ስምምነት የስራ አጋርነት ብቻ ሳይሆን የሁለቱን አገራት ወዳጅነት የሚያሳይ ነው ሲሉም ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ዘመናዊና ዘላቂነት ያለው የባቡር ትራንስፖርት ለማስፋፋት የሚያግዝ መሆኑን ገልጸው፤ ዘመናዊና ለአየር ንብረት ተስማሚ አረንጓዴ ትራንስፖርትን ለማስፋፋት የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በባቡር ዘርፍ የያዘችውን ራዕይ ለመደገፍ ጣሊያን ላሳየችው ቁርጠኝነት አመስግነው፤ ኢትዮጵያ በዘርፉ ከጣሊያን ጋር ያላትን ትብብር ለማጠናከር ዝግጁ መሆኗን አረጋግጠዋል። በኢትዮጵያ የጣሊያን አምባሳደር አጉሰቲኖ ፓልሴ(ዶ/ር)፤ ከኢትዮጵያ ጋር ያለን ወዳጅነት እንዲሁም በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ኢኮኖሚያዊ ግንኙነትን ለማሻሻል እንደሚሰራ ገልጸዋል። በባቡር ዘርፍ ያለንን የዳበረ ልምድ በማካፈል ከኢትዮጵያ ጋር በጋራ ለመስራት ዝግጁ ነን ብለዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል ሶስተኛውን የአስር ዓመት ዕቅድ ይፋ አደረገች
Sep 10, 2025 104
አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 5/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል ሶስተኛውን የአስር ዓመት ብሔራዊ በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ ዕቅድ ይፋ አደረገች። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ስብሰባ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል መካሄድ ከጀመረ ሶስተኛ ቀኑን ይዟል። በመርሀ ግብሩ የአፍሪካ የአየር ንብረት ተፅዕኖን ለመቀነስ በግብርና፣ አፈር ማዳበሪያ፣ ታዳሽ ሀይል፣ የአየር ንብረት ፋይናንስ እና ሌሎች ጉዳዮች ላይ በጋራ መስራት የሚያስችሉ ውይይቶች እየተደረጉ ነው። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር በዛሬው ዕለት የበካይ ጋዝ ልቀትን በመቀነስ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል ሶስተኛ የአስር ዓመት በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ ዕቅድ ይፋ አድርጓል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ፕሮጀክትቱን ይፋ ባደረጉበት ወቅት፤ በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ ዕቅድ በፓሪስ ስምምነት መሰረት በየአምስት ዓመቱ ማሻሻያ ይደረግበታል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ ዕቅድ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2025 እስከ 2035 የሚቆይ መሆኑን ገልጸዋል። ዕቅዱ ከኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር፣ ከሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው፣ ከ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ እና በረጅም ጊዜ የካርበን ልቀት ልማት ስትራቴጂ 2050 ጋራ የተጣጣመ መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር ከ2019 እስክ 2023 በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር አማካኝነት የደን ሽፋን ከ6 ነጥብ 4 ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ማለቱን ገልጸው፤ በ2030 ወደ 30 በመቶ ለማሳደግ ታቅዷል ብለዋል። የአስር ዓመቱ ዕቅድ የግብርና ምርታማነትን፣ የከተማ መሰረተ ልማትን፣ የታዳሽ ሀይል አቅርቦትን እና የሰብል ምርታማነትን ተጨባጭ በሆነ መንገድ የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል። በዶሮ እርባታ፣ ንብ በማነብ፣ በስጋ ምርት እንዲሁም በመስኖ ልማትና በሌሎች የግብርና ዘርፎች የተመዘገቡ ለውጦችን ማስቀጠል እንደሚችል ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለብዝሀ ህይወትና ሥነ ምህዳር ጥበቃ፣ የመሬት መሸርሸርን ለመከላከልና ጠንካራና ዘላቂነት ያለው ኢኮኖሚ ለመገንባት ከፌደራል ዓመታዊ በጀት እስከ አንድ በመቶ የሚሆነውን ትመድባለች ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ይጠይቃል ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፣ ዕቅዱን ለማሳካት 98 ነጥብ 35 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። በመሆኑም ለዕቅድ መሳካት ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ በፋይናንስ፣ በቴክኒክ እና በቴክኖሎጂ ዕገዛ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአየር ንብረት ፋይናንስ መፍትሔን በራስ አቅም መፍጠር እንደሚቻል አሳይቷል -የዓለም አቀፍ ተቋማት አመራሮች
Sep 9, 2025 198
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2017(ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአየር ንብረት ፋይናንስ መፍትሔን በራስ አቅም መፍጠር እንደሚቻል ያሳየ የአፍሪካ ፕሮጀክት መሆኑን የዓለም አቀፍ ተቋማት አመራሮች ገለጹ፡፡ ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ "ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፣ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል መካሄደ ከጀመረ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል፡፡ አፍሪካ ወደ ከባቢ አየር በካይ ጋዝ በመልቀቅ ከአራት በመቶ በታች ድርሻ ቢኖራትም ከፍተኛውን የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ጉዳት ታስተናግዳለች፡፡ ከፍተኛ የበካይ ጋዝ የሚለቁ ያደጉ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስን መሸፈን አለባቸው በሚል እሳቤ የፓሪስ ስምምነትን ጨምሮ የተለያዩ ውሳኔዎች ቢተላለፉም እስካሁን ከዚህ ግባ የሚባል ውጤት አልተገኘም፡፡ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን የአፍሪካ የአየር ንብረት ፖሊሲ ማዕከል አስተባባሪ ጀምስ ሙሮምበድዚ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ዓይነተ ብዙ ፋይዳ ያለው ፕሮጀክት ነው፡፡ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ለአየር ንብረት ፋይናንስ ችግር የራስን መፍትሔ ማበጀት የሚያስችል አዲስ የፋይናንስ ሞዴል መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ ኢትዮጵያ የጎረቤት ሀገራትን በታዳሽ ኃይል በማስተሳሰር ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ በመገንባት በአፍሪካ ቀዳሚ እንደሚያደርጋት ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርና በታዳሽ ኃይል ልማት ያስመዘገበችው ስኬት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ማስተማሪያ እንደሚሆንም አንስተዋል፡፡ የዓለም የእርሻና ምግብ ድርጅት ረዳት ዳይሬክተር ጀነራል እና የአፍሪካ ተጠሪ አበበ ኃይለገብርኤል (ዶ/ር) በበኩላቸው፥ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ከተባበርን ተዓምር እንደምንሰራ የተማርንበት የመቻል ምልክት ነው ብለዋል፡፡ ትራንስፖርት፣ ንግድና ኢንቨስትመንት፣ ግብርና ሜካናይዜሽን፣ ቴክኖሎጂና ሌሎች መሰረታዊ አገልግሎቶች ከኃይል ጋር የተሳሰሩ መሆናቸውን ገልጸው፤ ለአየር ንብረት ለውጥ መፍትሔ እንደሚሆን ጠቅሰዋል፡፡ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ታዳሽ ኃይል በማምረት የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ከመከላከል ባለፈ የአየር ንብረት ፋይናንስ ምንጭ ሆኖ ያገለግላል ነው ያሉት፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ ከበለጸጉ ሀገራት መምጣት አለበት የሚለው ውጤት እንዳላመጣ በመጥቀስ፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ የአየር ንብረት ፋይናንስን በራስ አቅም ማመንጨት እንደሚቻል ለሌሎችም ትምህርት የሰጠ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተጽዕኖን ለመከላከል የጋራ ትብብርን ማጠናከር ይገባል
Sep 8, 2025 269
አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 3/2017(ኢዜአ)፦በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ እያደረሰ ያለውን አሉታዊ ተጽዕኖ ለመከላከል የጋራ ትብብርን ማጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ "ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፣ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። በጉባኤው መክፈቻ የታደሙት የተለያዩ አገራት መሪዎችም በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተጽዕኖን ለመከላከል የጋራ ትብብርን ማጠናከር ወሳኝ ነው ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሃሙድ አሊ የሱፍ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የአየር ንብረት ለውጥ አፍሪካን በብዙ እየፈተነ ይገኛል። ይህን ዓለምአቀፋዊ ተግዳሮት ለመከላከል አህጉሪቷ የተለያዩ ጥረቶችን እያደረገች መሆኗንም አንስተዋል። ይሁንና አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተጽዕኖን ለመከላከል የምታደርገው ጥረት በቂ የፋይናንስ፣ የቴክኖሎጂና የባለሙያ ድጋፍ እያገኘ አለመሆኑን ነው የተናገሩት። አፍሪካ ለዓለም አየር ንብረት ለውጥ ያላት ድርሻ አነስተኛ መሆኑን ያስታወሱት የኮሚሽን ሊቀ መንበር መሃሙድ፤ ሆኖም የችግሩ ዋነኛ ገፈት ቀማሽ መሆኗን አመልክተዋል። አህጉሪቷ ዓለምአቀፉን የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል ለምታደርገው ጥረት ሁለንተናዊ የፋይናንስ ድጋፍ ማድረግ ፍትህን የማረጋገጥ ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል። የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ በጉባኤው መክፈቻ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ከሁለት ዓመታት በፊት በናይሮቢ በተካሄደው የመጀመሪያው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባኤ አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ የመፍትሄው አካል ለመሆን በቁርጠኝነት እንደምትሰራ አቅጣጫ ማስቀመጧን አስታውሰዋል። አህጉሪቷ የችግሩ ዋነኛ ተጎጂ እንደመሆኗ ጉዳቱን አስቀድሞ ለመከላከል አሰላለፏን መቀየር ይገባታል ነው ያሉት። በአፍሪካ ለአየር ንብረት ተስማሚ ኢኮኖሚ ለመገንባት አገራት የተለያዩ ጥረቶችን እያደረጉ መሆኑንም ተናግረዋል። ይሁንና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል አገራት የሚያደርጉት ጥረት ውጤታማ እንዲሆን ዓለምአቀፍ ትብብርን ማጠናከር ይገባል ብለዋል። አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እያደረገች ያለውን ጥረት በዓለምአቀፍ መድረኮች ለማስተጋባት የተቀናጀና የተናበበ የጋራ ሥራ መስራት የሚጠይቅ መሆኑንም ተናግረዋል። የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሐሰን ሼክ መሀሙድ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ መንግስት በአዲስ አበባ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ እንድንመክር መድረክ ስላዘጋጀ ምስጋና ይገባዋል ብለዋል። አገራቸው ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ያላት አስተዋፅኦ አነስተኛ ቢሆንም ከፍተኛ ጉዳት እያስተናገደች እንደምትገኝ ገልጸዋል። በመሆኑም በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በሚደረገው ጥረት ሶማሊያ ትብብሯን አጠናክራ ቀጥላለች ብለዋል። ለዚህም ፖሊሲ በመቅረጽና ተቋማዊ ማዕቀፍ በማዘጋጀት እንዲሁም የአረንጓዴ አየር ንብረት ፈንድ በማቋቋም የተግባር እንቅስቃሴ መጀመሩን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም አፍሪካዊ መፍትሔ ማምጣት እንደሚቻል በተግባር አሳይታለች
Sep 8, 2025 259
አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 3/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ፣ በሌማት ትሩፋትና በህዳሴ ግድብ ለአየር ንብረት ለውጥ አፍሪካዊ መፍትሔ ማምጣት እንደሚቻል በተግባር ማሳየቷን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ "ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሔዎችን ማፋጠን፤ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት የሚካሄደው የሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ጀምሯል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት ባደረጉት ንግግር፣ ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ አፍሪካውያን አፍሪካዊ መፍትሔ የምናዘጋጅበት ነው ብለዋል፡፡ በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ የህልውና ጉዳይ መሆኑን በመግለጽ፣ በትብብር የምንሰራበት ጊዜ አሁን ነው ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ አንገብጋቢ ጉዳይ መሆኑን በመግለጽ፤ አፍሪካ የቴክኖሎጂ፣ የፋይናንስ እና የጊዜ እጥረት እንዳለባት ተናግረዋል። አፍሪካ ታዳሽ ሀይል፣ ሰፊ የሚታረስ መሬት፣ ውሀና ጸሀይ ሀይል ያላት አህጉር መሆኗን በመጥቀስ፣ ለችግሮቹ መፍትሔ ለማበጀት ትብብርን ማጠናከር ይገባል ብለዋል። ስብሰባው በህልውናችን ላይ ለመምከር ሳይሆን የመፍትሔ አቅጣጫዎችን የምናስቀምጥበት ወሳኝ ወቅት ነው ብለዋል። ዓለም አቀፍ አጋሮቻችን እርዳታ እንደማንፈልግ እንዲያውቁልን እንፈልጋለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ባለራዕዮች በመሆናችን ከእኛ ጋር ሊያለሙ ይገባል ብለዋል፡፡ ራዕዩን ወደ ተግባር ለመቀየር የአፍሪካ የአየር ንብረት ኢኖቬሽን ኮምፓክት ይፋ እንዲሆን ሀሳብ አቅርበዋል፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም አፍሪካዊ መፍትሔዎችን ገቢራዊ ማድረግ ይገባል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ኢትዮጵያ ምሳሌ የሚሆኑ ተግባራዊ እርምጃ እየወሰደች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ በ2019 በጀመረችው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ባለፉት ሰባት ዓመታት ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መትከሏን አንስተዋል፡፡ በዚህም ከውጭ የሚገባውን የስንዴ ምርት ማስቀረት፣ የአካባቢን ስነ ምህዳር መጠበቅ እና የአረንጓዴ ልማትን ማሳደግ ችላለች ብለዋል። አፍሪካ ከንግግር ያለፈ የሚጨበጥ የተግባር እርምጃ ያስፈልጋታል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ኢትዮጵያ ከውጭ የሚገባውን ምርት በመቀነስ የገጠሩን ማህበረሰብ ገቢ ማሳደግ ችላለች ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በመገንባት በቅርቡ እንደምታስመርቅ የጠቀሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ከአምስት ሺህ ሜጋ ዋት በላይ የኤሌክትሪክ ሀይል ማመንጨት እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ እነዚህ ኢኒቬቲቮች ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በራሷ የወሰደቻቸው የመፍትሔ ርምጃዎች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ፣ በሌማት ትሩፋትና ህዳሴ ግድብን በመገንባት የአየር ንብረት ለውጥ አፍሪካዊ መፍትሔ ማምጣት እንደሚቻል በተግባር አሳይታለች ብለዋል፡፡
አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የምታደርገውን ጥረት በፋይናንስ መደገፍ ፍትህን የማረጋገጥ ጉዳይ ነው- መሀሙድ አሊ የሱፍ
Sep 8, 2025 171
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2017(ኢዜአ)፦አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የምታደርገውን ጥረት በፋይናንስ መደገፍ ፍትህን የማረጋገጥ ጉዳይ መሆኑን የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀሙድ አሊ የሱፍ ገለጹ። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ "ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፣ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። ኢትዮጵያና የአፍሪካ ህብረት በጋራ ባዘጋጁት ጉባኤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)ን ጨምሮ የተለያዩ አገራት መሪዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ ምሁራንና ተመራማሪዎች፣ የአለምአቀፍና አህጉራዊ ተቋማት ተወካዮችን ጨምሮ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ታድመዋል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሃሙድ አሊ የሱፍ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፣ የአየር ንብረት ለውጥ አፍሪካን በብዙ እየፈተነ ይገኛል። ይህን አለምአቀፋዊ ተግዳሮት ለመከላከል አህጉሪቷ የተለያዩ ጥረቶችን እያደረገች መሆኗንም አንስተዋል። ይሁንና አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተጽዕኖን ለመከላከል የምታደርገው ጥረት በቂ የፋይናንስ የቴክኖሎጂና የባለሙያ ድጋፍ እያገኘ አለመሆኑን ነው የተናገሩት። አፍሪካ ለዓለም አየር ንብረት ለውጥ ያላት ድርሻ አነስተኛ ቢሆንም የችግሩ ዋነኛ ገፈት ቀማሽ መሆኗንም አመልክተዋል። አህጉሪቷ አለምአቀፉን የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል ለምታደርገው ጥረት ሁለንተናዊ የፋይናንስ ድጋፍ ማድረግ ፍትህን የማረጋገጥ ጉዳይ ነው ብለዋል። በሁለተኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ አፍሪካውያን በአየር ንብረት ለውጥ ላይ ድምጻቸውን በጋራ ከማሰማት ባለፈ ለመፍትሔው በግንባር ቀደምነት መስራት እንዳለባቸውም ነው ሊቀመንበሩ ያሳሰቡት።
ጉባኤው አፍሪካ በዓለም አቀፍ መድረክ በአንድ አቋም ድምጿን የምታሰማበት ውሳኔ የሚተላለፍበት ነው- ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር)
Sep 8, 2025 138
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2017(ኢዜአ)፦ሁለተኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ስብሰባ አፍሪካ በዓለም አቀፍ መድረክ በአንድ አቋም ድምጿን የምታሰማበት ውሳኔ የሚተላለፍበት እንደሚሆን የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) ገለጹ። የሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል መካሄድ ጀምሯል። በመርሀ ግብሩ ላይ የኢፌደሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፣ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሀሙድ አሊ የሱፍ፣ የኬንያ ፕሬዝዳንት ዊሊያም ሩቶ፣ የጅቡቲ ፕሬዝዳንት እስማኤል ኦማር ጌሌ፣ የሶማሊያ ፕሬዝዳንት ሀሰን ሼክ መሀሙድ፣ የእስዋቲኒ ጠቅላይ ሚኒስትር ሩስል ምሚሶ ድላሚኒ እንዲሁም ዓለም አቀፋዊና አህጉራዊ ተቋማት ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ስብሰባው አፍሪካ በቀጣይ ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤዎች የጋራ አቋም እንዲኖራት የሚያስችል ነው። በሁለተኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ስብሰባ አፍሪካ አህጉራዊ መፍትሔዎች ላይ ውይይት የሚደረግበት መሆኑን ገልጸዋል። ስብሰባውን ለማዘጋጀት ብሔራዊ ኮሚቴ ተቋቁሞ እንደነበር ገልጸው፤ የአዲስ አበባ የመሪዎች ቃል ኪዳን በቀጣይ ኮፕ-30 ጉባኤ አፍሪካ በአንድ አቋም ድምጿን የምታሰማበት መሆኑን ገልጸዋል። ከዛሬ ጀምሮ በቀጣዮቹ ሶስት ቀናት ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን፣ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ ተጠቃሚነት፣ ቅድመ ማስጠንቀቂያ እና አፍሪካ መር መፍትሔዎች ውይይት ይደረግባቸዋል።
በዓለምአቀፍ መድረኮች የአፍሪካን ድምጽ ለማስተጋባት የተቀናጀና የጋራ ሥራ ይጠይቃል - የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ
Sep 8, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2017(ኢዜአ)፦በዓለምአቀፍ መድረኮች የአፍሪካን ድምጽ ለማስተጋባት የተቀናጀና የተናበበ የጋራ ሥራ እንደሚጠይቅ የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ገለጹ። ሁለተኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባኤ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። በጉባኤው መክፈቻ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)ን ጨምሮ የአገራት መሪዎች የዓለም አቀፍና አህጉራዊ ተቋማት ኃላፊዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ ምሁራንና ተጽዕኖ ፈጣሪ ግለሰቦች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል። የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ በጉባኤው መክፈቻ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ከሁለት ዓመታት በፊት በናይሮቢ በተካሄደው የመጀመሪያው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባኤ አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ የመፍትሄው አካል ለመሆን በቁርጠኝነት እንደምትሰራ አቅጣጫ ማስቀመጧን አስታውሰዋል። አህጉሪቷ የችግሩ ዋነኛ ተጎጂ እንደመሆኗ ጉዳቱን አስቀድሞ ለመከላከል አሰላለፏን መቀየር ይገባታል ነው ያሉት። በአፍሪካ ለአየር ንብረት ተስማሚ ኢኮኖሚ ለመገንባትና ግብርናና ኢንዱስትሪን ለአየር ንብረት ተስማሚ ለማድረግ አገራት የተለያዩ ጥረቶችን እያደረጉ መሆኑንም ተናግረዋል። ይሁንና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል አገራት የሚያደርጉት ጥረት ውጤታማ እንዲሆን ዓለምአቀፍ ትብብርን ማጠናከር ይገባል ብለዋል። አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እያደረገች ያለውን ጥረት በዓለምአቀፍ መድረኮች ለማስተጋባት የተቀናጀና የተናበበ የጋራ ሥራ መስራት የሚጠይቅ መሆኑንም ተናግረዋል። የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስሮችን በማጠናከር የአየር ንብረት ለውጥን በዘላቂነት መከላከል የሚያስችሉ ኢንቨስትመንቶችን መሳብ ያስፈልጋል ብለዋል። የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሐሰን ሼክ መሀሙድ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ መንግስት በአዲስ አበባ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ እንድንመክር መድረክ ስላዘጋጀ ምስጋና ይገባዋል ብለዋል። አገራቸው ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ያላት አስተዋፅኦ አነስተኛ ቢሆንም ከፍተኛ ጉዳት እያስተናገደች እንደምትገኝ ገልጸዋል። በመሆኑም በአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በሚደረገው ጥረት ሶማሊያ ትብብሯን አጠናክራ ቀጥላለች ብለዋል። ለዚህም ፖሊሲ በመቅረጽና ተቋማዊ ማዕቀፍ በማዘጋጀት እንዲሁም የአረንጓዴ አየር ንብረት ፈንድ በማቋቋም የተግባር እንቅስቃሴ መጀመራቸውን ተናግረዋል።
አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ የምትሻው እርዳታ ሳይሆን የጋራ ኢንቨስትመንት ነው-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Sep 8, 2025 102
አዲስ አበባ፤ጳጉሜን 3/2017(ኢዜአ)፦አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ የምትሻው እርዳታ ሳይሆን የጋራ ኢንቨስትመንት ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተናገሩ። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል መካሄድ ጀምሯል። በጉባኤው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)ን ጨምሮ የቀጣናውና የተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች፣የዓለም አቀፍ ተቋማት መሪዎች እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥ ተመራማሪዎች ተሳትፈዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጉባኤው መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር፣ የአየር ንብረት ለውጥ ፈተናን ለመቋቋም ከጎደለን ሳይሆን ካለን መጀመር አለብን ብለዋል። ከዚህ አኳያ አፍሪካ በርካታ የወጣቶች ቁጥር፣ መልማት የሚችል መሬት እንዲሁም ለታዳሽ ሃይል የሚሆን በርካታ አቅም አላት ነው ያሉት። በመሆኑም እዚህ የተገኘነው የዓለምን የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄ ለመቀየስ ነው ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በመሆኑም አፍሪካ ስነ ምህዳሯን ሳትጎዳ ማደግ እንደምትችል አብራርተዋል። አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ የምትሻው እርዳታ ሳይሆን የጋራ ኢንቨስትመንት ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የሚደረግ ኢንቨስትመንት ፋይዳው ጉልህ መሆኑን አንስተዋል። አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ ዋነኛዋ መፍትሄ አመንጪ መሆን እንዳለባትም ተናግረዋል። አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የራሷ የመረጃ ሉዓላዊነት ሊኖራት እንደሚገባም አንስተዋል። የአህጉሪቷ ዩኒቨርሲቲዎችና ተመራማሪዎች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈና ለአየር ንብረት ለውጥ የተደራጀ መፍትሄ የሚያቀርብ ማዕቀፍ እንዲቋቋምም ሃሳብ አቅርበዋል። ከዚህ አኳያ ኢትዮጵያ ከ7 ዓመት በፊት በጀመረችው የአረንጓዴ አሻራ አማካኝነት ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መትከሏንም ጠቁመዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከባቢን ከመጠበቅ ባሻገር የተጎዱ ከባቢዎች እንዲያገግሙ፣ ለምግብ ዋስትና እና ለስራ እድል ፈጠራ ትልቅ እድል መፍጠሩን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ከአየር ንብረት ለውጥ ችግር መፍትሄ ጋር የተጣጣመ የመስኖ ልማት በማካሄድም በስንዴ ምርት ከፍተኛ ለውጥ ማምጣቷን አብራርተዋል። በቅርቡ የሚመረቀው ታላቁ የህዳሴ ግድብም ከ5 ሺህ ዋት በላይ ታዳሽ ሃይል በማመንጨት ኢትዮጵያንና ቀጠናውን በሃይል ተጠቃሚ እንደሚያደርግ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ማስተናገድ እንደምትሻም ጠቁመዋል።
የአየር ንብረት ለውጥ በታዳጊ ሀገራት ላይ የሚያደርሰውን ተጽዕኖ መቀነስ የሚያስችል የፋይናንስ ድጋፍ ማጠናከር ያስፈልጋል
Sep 8, 2025 107
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2017(ኢዜአ)፦የበለጸጉ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ በታዳጊ ሀገራት ላይ የሚያደርሰውን ተጽዕኖ መቀነስ የሚያስችል የፋይናንስ ድጋፍ ማጠናከር እንደሚኖርባቸው የጀርመን የአካባቢ፣ የአየር ንብረት፣ የተፈጥሮ ጥበቃ እና የኒውክሌር ደህንነት ሚኒስቴር ስቴት ሴክሬታሪ ዮህን ፍልስባርትዝ ገለጹ። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ "ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፣ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። በጀርመን የኢኮኖሚ ትብብርና ልማት ሚኒስቴር የፓርላሜንታሪ ስቴት ሴክሬታሪ ቤርብል ኮፍለር (ዶ/ር) የተመራ ከፍተኛ የጀርመን ልዑካን ቡድን በሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ላይ እየተሳተፈ ነው። በኢትዮጵያ የጀርመን ኤምባሲ ለልዑክ ቡድኑ የአቀባበል መርሃ ግብር አካሂዷል። በመርሃ ግብሩ መክፈቻ ላይ የጀርመን የአካባቢ፣ የአየር ንብረት፣ የተፈጥሮ ጥበቃ እና የኒውክሌር ደህንነት ሚኒስቴር ስቴት ሴክሬታሪ ዮህን ፍልስባርትዝ እንደተናገሩት፤ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ዓለም አቀፍ ትብብርን ማጠናከር ያስፈልጋል። ለአየር ንብረት ተስማሚ የሆነ የኢኮኖሚ ስርዓትን ማጠናከር ተገቢ መሆኑን ጠቅሰው አፍሪካውያን በወንድማማችነት መንፈስ ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በትብብር መስራት ይገባቸዋል ብለዋል። በጀርመን የኢኮኖሚ ትብብርና ልማት ሚኒስቴር የፓርላሜንታሪ ስቴት ሴክሬታሪ ቤርብል ኮፍለር (ዶ/ር) በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ በታዳጊ ሀገራት የኢኮኖሚ ሥርዓት ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደረ ይገኛል። ለአየር ንብረት ሥነ-ምህዳር የሚስማማ የኢኮኖሚ ስርዓትን ለመገንባት ከቃል የዘለለ ተግባራዊ እርምጃ መውሰድ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ታዳጊ አገራት ለአየር ንብረት ተስማሚ የኢኮኖሚ ሥርዓት እንዲገነቡ መደገፍ እንደሚገባም ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የጀርመን ምክትል አምባሳደር ፈርዲናንድ ፎን ቫሄ (ዶ/ር)፤ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋምና ወደ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመሸጋገር የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የሚያመልክቱ ለውጦች መኖራቸውን አንስተዋል። በፀሀይ ሀይል፣ በሀይድሮ ፓወር፣ በንፋስና በእንፋሎት የሚሰሩ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች እየተበራከቱ መምጣታቸው በአዎንታዊነት የሚጠቀስ መሆኑንም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የምታስተናግደው 2ኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባዔ ሀገራችንያሳካቻቸውን ተጨባጭ ልምዶች የምታካፍልበት መድረክ ነው - የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
Sep 8, 2025 81
2ኛዉ የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ይህንን ጉባኤ የምታስተናግደው ለተሳታፊዎች ተጨባጭ ልምዶችን በማካፈል ጭምር ነው፡፡ ኢትዮጵያ ባለፉት ሰባት ዓመታት ብቻ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እየሠራች ትገኛለች፡፡ መላው ኢትዮጵያውያን በተከታታይ ዓመት በሚያደርጉት የላቀ ተሳትፎ የራሳቸውን ክብረ ወሰን እያሻሻሉ በአንድ ጀምበር ከ700 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን መትከል ችለዋል፡፡ ይህም ለዓለም ትምህርት መኾን የሚችል ተነሣሽነትና ቁርጠኝነት ነው፡፡ ኢትዮጵያ ነባር ከተሞችን በማዘመን የውኃ ብክለትን ለመቆጣጠር በሰፊው እየሠራች ነው፡፡ የአዲስ አበባ የወንዞች ዳርቻ ልማትን ብቻ ብንወስድ ከእንጦጦ ከፍተኛ ቦታዎች የሚነሡ የአዋሽ ተፋሰስ ገባር ወንዞችን በተሳካ ኹኔታ እያከመች ነው፤ ይህም አጠቃላይ የአዋሽ ወንዝን የማከም አካል ተደርጎ የሚወሰድ ትልቅ ትምህርት ነው፡፡ ወንዞቻችን ንጹሕ፣ ማራኪና ለመናፈሻነት የሚመረጡ እንዲኾኑ በትኩረት መሥራታችን ለሌሎች አገራት በትልቁ አስተማሪ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ታዳሽ ኃይልን በልዩ ትኩረት በማምረትና በመጠቀምም አብነት መኾን የምትችል ሀገር ናት፡፡ ከተሞቿ እና ኢንዱስትሪዎቿ በስፋት የሚጠቀሙት ኃይል ከውኃ፣ ከነፋስ እና ከፀሐይ ኃይል የሚመነጭ ነው፡፡ ከራሷ አልፋ ሌሎች የቀጣናውን ሀገራት የታዳሽ ኃይል ተጠቃሚ በማድረግም ለአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ጉልህ ሚና የምትጫወት ሀገር ናት፡፡ ኢትዮጵያ የምታመነጫውን ታድሽ ኃይል ለጎረቤት ሀገራት በማጋራት መሰረተ ልማትና በኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴም በቀጣናው ሀገራት መካከል ትስስርና ቅንጅት እየፈጠረች ነው፡፡ እንደ ጂቡቲ፣ ሱዳን፣ ኬንያ፣ እና ታንዛንያ ያሉ አገራት ከኢትዮጵያ ታዳሽ ኃይል ተጠቃሚ ከኾኑ ሀገራት መካከል ተጠቃሽ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ታዳሽ ኃይልን በስፋት በመጠቀሟ ለማገዶ ሲባል የሚጨፈጨፍ ደንን በእጅጉ ቀንሳለች፡፡ የበካይ ጋዝ ምንጭ ተጠቃሚ ተሽከርካሪዎችን መጠን ለመቀነስ እና በሂደትምበታዳሽ ኃይል ተጠቃሚ ተሽከርካሪዎች ለመተካት በስፋት እየሠራች ነው፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ብቻ ከ100 ሺህ በላይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች አገልግሎት እየሰጡ ነው፡፡ መንግሥት በልዩ ልዩ ማበረታቻዎች ኹሉም የተሽከርካሪ ባለቤቶች ወደ ታዳሽ ኃይል ተጠቃሚነት እንዲገቡ እየሠራ ነው፤ ይህም በጉባኤዉ ተሳታፊዎች ልምድ እንደሚወሰድበት ይጠበቃል፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤን ስታስተናግድ ጉባኤዉ ተጨባጭ ለውጥ የሚያመጡ ሐሳቦች የሚንሸራሸሩበት፣ አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ አስተዋጽኦዋ ኢምንት ኾኖ በጉዳቱ ክፉኛ እየተጎዳች መኾኑ ታውቆ የማካካሻ እና የማስተካከያ እርምጃ የሚወሰድበት እንዱኾን አበክራ ትሠራለች፡፡ ኢትዮጵያውያን የእንግዳ ተቀባይነት ባህል ቢኖረንም አፍሪካውያን ወንድሞቻችንና እህቶቻችንን ደግሞ እንደ ቤተሰብ በማስተናገድ ቆይታቸው ያማረ እና ፍሬያማ እንዲኾን እናደርጋለን፡፡ ጳጉምን 3/2017 ዓ/ም የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
2ኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባኤ ዛሬ ይጀመራል
Sep 8, 2025 83
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 3/2017(ኢዜአ)፦ ሁለተኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባኤ ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት በአዲስ አበባ ይካሄዳል። ጉባኤው "ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማሳለጥ፣ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት በአዲስ አበባ ይካሔዳል። ከዋናው ጉባዔ አስቀድሞ ባለፉት ጥቂት ቀናት ቅድመ ጉባዔዎቹ በተሳካ ሁኔታ መካሄዳቸውንና ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ ሀሳቦች መነሳታቸው ተገልጿል። ኢትዮጵያም የአየር ንብረት ለውጥ ችግርን በጋራ መከላከል የተሻለ ውጤት ለማምጣት ያላትን አቋም እና ያከናወነቻቸውን ተግባራት በጉባኤው ታንፀባርቃለች። በጉባኤው አካባቢያዊ መፍትሄዎችን ከአህጉራዊ የአየር ንብረት ስትራቴጂዎች ጋር ማስተሳሰር በሚቻልበት ሁኔታዎች ላይ ምክክር ይደረጋል። አፍሪካውያን የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በቁርጠኝነት የሚሰሩበት የ"አዲስ አበባ ድንጋጌ ስምምነት"በጉባዔው እንደሚጸድቅ ይጠበቃል። አፍሪካ በአየር ንብረት አስተዳደር ትክክለኛ ቦታ ለመያዝ የምታደርገውን ጥረት የሚያግዙ ውሳኔዎች ይተላለፋሉ ተብሎም ይጠበቃል። በጉባዔው የተለያዩ ሀገራት መሪዎችን ጨምሮ ከ25ሺ በላይ ተሳታፊዎች ይታደማሉ።