አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
የተፋሰስ ልማት ስራ ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው - ግብርና ሚኒስቴር
Feb 14, 2025 47
አዲስ አበባ፤ የካቲት 7/2017(ኢዜአ)፡- ባለፉት አመታት በተከናወነው የተፋሰስ ልማት ስራ እንደ ሀገር ተጨባጭ ውጤት እየተገኘ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። በተያዘው አመት ህብረተሰቡን በንቃት ባሳተፈ መልኩ ከጥር 6 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ በይፋ መጀመሩ የሚታወስ ነው። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ ፋኖሴ መኮንን እንደገለጹት በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ ክስተቶች ምክንያት የሀገሪቱ መሬት ለጉዳት ተጋላጭ ነው፡፡ መንግስት ይህንን ከግንዛቤ በማስገባት የተፋሰስ ልማት ስራዎች በየግዜው በትኩረት እንዲከናወኑ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ተከትሎ በተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ስራዎች ተጨባጭ ለውጥ እየተመዘገበ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በተሰሩ ስራዎች በኢትዮጵያ በየዓመቱ የሚከሰተውን የአፈር መሸርሸር በከፍተኛ መጠን መቀነስ መቻሉን ገልጸዋል። በ2017 ዓ.ም የበጋ ወቅት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ በሁሉም በሀገሪቱ በርካታ አካባቢዎች ለማከናወን ወደ ተግባር መገባቱንም ተናግረዋል፡፡ የተፋሰስ ልማት ስራው በሀገር አቀፍ ደረጃ በጥር 2017 ዓ.ም የተጀመረ መሆኑን ጠቅሰው፤ በአሁኑ ወቅት ሁሉም ክልሎች ወደ ተግባር መግባታቸውን ገልጸዋል። አጠቃላይ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራዎቹ በአብዛኞቹ አካባቢዎች መጋቢት አጋማሽ ድረስ ይጠናቀቃል ተብሎ እንደሚጠበቅም ጠቅሰዋል። አቶ ፋኖሴ አክለውም የተፈጥሮ ሀብትን የመጠበቅ፣ የመንከባከብና የማልማት ተግባር ለነገ የማይባል ጉዳይ በመሆኑ ተጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው አጽንኦት ሰጥተዋል። ሀገሪቱ ያላትን የተፈጥሮ ሀብት ፀጋዎችን ለመጠበቅ በሚሰራው ስራ ህብረተሰቡ በተለያዩ አካባቢዎች በሚከናወኑ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ አጠናክሮ ሊቀጥሉ እንደሚገባም ተናግረዋል።
ዓለም አቀፉ የመስኖ ልማትና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ምርታማነት ጉባኤ እየተካሔደ ነው
Feb 12, 2025 91
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ የምታስተናግደው ዓለም አቀፍ የመስኖ ልማትና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ምርታማነት ጉባኤ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። በጉባኤው ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ፣ የቀድሞ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)፣ የአፍሪካ ሀገራት የቀድሞ መሪዎች፣ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎችን ጨምሮ በርካታ ተሳታፊዎች ታድመዋል። በመስኖና ቆላማ አከባቢ ሚኒስቴር የተዘጋጀው ይህ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ዛሬን ጨምሮ ለሶስት ቀናት የሚካሄድ ይሆናል። በጉባኤው በመስኖ ልማት፣ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን መከላከል ዙሪያ ዓለም አቀፍ ልምዶችና ተሞክሮዎች ይቀርባሉ ተብሏል። ጉባኤው የአየር ንብረት ተለዋዋጭነትን በመቋቋም የተሻሻለ የኑሮ ዘይቤ እና የመስኖ ልማትን ለማጎልበት ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑም ተጠቁሟል። ኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ያከናወነቻቸው ተግባራት በተለይም በበጋ መስኖ ስንዴ ልማትናአረንጓዴ አሻራ ዙሪያ ያላትን ልምድ እንደምታጋራም ይጠበቃል። በጉባኤው የመስኖ ስራዎችን የሚያሳይ ኤግዚቢሽን በይፋ ተከፍቷል።
በሃላይደጌ አሰቦት ዕጩ ብሔራዊ ፓርክ ተከስቶ የነበረው ሰደድ እሳት ሙሉ ለሙሉ ጠፍቷል
Feb 11, 2025 105
ሰመራ፤ የካቲት 4/2017 (ኢዜአ)- በሃላይደጌ አሰቦት ዕጩ ብሔራዊ ፓርክ ተከስቶ የነበረው ሰደድ እሳት በከፍተኛ ርብርብ መጥፋቱን የብሔራዊ ፓርክ ፅህፈት ቤቱ አስታወቀ። የፓርኩ ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አህመድ ኢድሪስ፤ ላለፉት አራት ቀናት በፓርኩ ላይ የተከሰተውን እሳት ለማጥፋት ከፍተኛ ጥረትና ርብርብ ሲደረግ መቆየቱን ገልጸዋል። በዚህም በዛሬው እለት እሳቱን ሙሉ ለሙሉ በመቆጣጠር ማጥፋት መቻሉን ተናግረዋል። የእሳት አደጋው መንስኤና የደረሰው የጉዳት መጠን በቀጣይ ተለይቶ ይፋ የሚደረግ መሆኑን አንስተው በአብዛኛው ግን በሳሩ ላይ ከ200 እሰከ 400 ሄክታር ቃጠሎ መድረሱን ተመልክተናል ብለዋል። ሰደድ እሳቱን ለመቆጣጠር በተለይም የዱር እንሰሳት ጥበቃ ባለ ስልጣን፣የገቢ ራሱ ዞን እና አሚባራ ወረዳ ነዋሪዎችና አመራሮች ፣የአዋሽ ብሄራዊ ፓርክ እንዲሁም የሃላይደጌናአንዲዶ ቀበሌ ነዋሪዎች ላደረጉት ብርቱ ጥረትና ርብርብ ኀላፊው አመስግነዋል። ከ1965 ዓ.ም. ጀምሮ ጥብቅ ደን የነበረውና በኋላም የሃላይደጌ አሰቦት ዕጩ ብሔራዊ ፓርክ የሚል ስያሜ ያገኘው ፓርክ በውስጡ የሜዳ አህያ፣ ሳላና የሜዳ ፍየልን ጨምሮ የተለያዩ እንስሳትና የአዕዋፋት ዝርያዎች እንዳሉት ይታወቃል።
በትግራይ ክልል እየተከናወነ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በጥሩ ተሞክሮነት የሚወሰድ ነው
Feb 10, 2025 109
መቀሌ፤ የካቲት 3/2017(ኢዜአ)፡- በትግራይ ክልል እየተከናወነ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በጥሩ ተሞክሮነት የሚወሰድ መሆኑ ተገለጸ። የግብርና ሚኒስቴርና የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የዘርፉ የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም ባለሙያዎች በክልሉ እየተከናወነ ያለውን የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በኃውዜን ወረዳ እና በሌሎች አካባቢዎች ተዘዋውረው ተመልክተዋል። ከጉብኝቱ ተሳታፊዎች መካከል በግብርና ሚኒስቴር የዘላቂ ልማትና የመሬት አያያዝ የክትትልና ድጋፍ ከፍተኛ ባለሙያ ፈታ ዘበርጋ፤ እየተከናወነ ያለው ስራ አስደናቂ በመሆኑ ለሌሎች አካባቢዎችም ጥሩ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው በርካቶችን ባሳታፈ መልኩ በአጭር ጊዜ በጥራትና በፍጥነት መሰራቱንም አድንቀዋል። በመሆኑም በክልሉ እየተከናወነ ያለው የተቀናጀና አሳታፊ የሆነ የልማት ስራ ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት መሆኑን አንስተዋል። በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የእርሻና ተፈጥሮ ኃብት ቢሮ ምክትል ቢሮ ሃላፊ አለምብርሀን ሀሪፈዮ፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን ተናግረዋል። በዘንድሮው የልማት መርሃ ግብር ከ62 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የሚከናወንበት መሆኑንም አረጋግጠዋል። በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው በተለይም የክልሉ አርሶ አደሮች በስፋት እየተሳተፉ መሆኑን ጠቅሰው በተጠናከረ መልኩ ይቀጥላል ብለዋል። በሐውዜን ወረዳ በልማት ስራው ላይ ከተገኙት አርሶ አደሮች መካከል ወይዘሮ ፅገ ገብረ ክርስቶስ እና አቶ ዳንኤል ገብረ ኪዳን፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው ለአርሶ አደሩ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው መሆኑን በመገንዘብ ጠንካራ ተሳትፎ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ የሚደነቅ ነው - ዓለም አቀፍ ተቋማት
Feb 10, 2025 97
አዲስ አበባ፤ የካቲት 03/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባት የሰጠችው ትኩረት የሚደነቅ መሆኑን ዓለም አቀፍ ተቋማት ገለጹ። በተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ ቀጣናዊ የትብብር ማዕከል የካርቦን ግብይት ስፔሻሊስት አርባንስ ቤኒዋኒራ፤ ኢትዮጵያ አየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቀነስ ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ ሚናዋን እየተወጣች ነው ብለዋል። የ2015ቱ የፓሪስ ስምምነት አንቀፅ-6 ለዓለም አቀፍ የካርበን ገበያና የልቀት ቅነሳ ትብብር ስትራቴጂ ማዕቀፍ መነሻ ነው ብለዋል። በተማከለና በሁለትዮሽ ስምምነት ሀገራት የአየር ንብረት ኢላማን ለማሳካት ተግባራዊ የሚያደርጉት የአሰራር ሥርዓት የሚመራውም በዚሁ አንቀጽ መሰረት እንደሆነ አስታውሰዋል። ኢትዮጵያም የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቀነስ በአረንጓዴ አሻራና በታዳሽ የኃይል አማራጭ ዘርፍ ስኬታማ አረንጓዴ ኢኮኖሚ እየገነባች መሆኗ የሚደነቅ ነው ብለዋል። ለሞተር አልባና በኤሌክትሪክ ለታገዘ የትራንስፖርት ስርዓት ትኩረት መስጠቷ ለዓለም አቀፍ ስምምነቶች ትግበራና ለበካይ ጋዝ ልቀት ቅነሳ ያላትን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይም አንስተዋል። ለአየር ንብረት ለውጥ የማይይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ማሳያ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአየር ንብረት ዙሪያ ጥናትና ማማከር ላይ የተሰማራው የክላይሜት ፐርሰፕሽን ግሩፕ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ስቴፈን ኖክ፥ በሞሮኮ እ.አ.አ በ2016 በተካሄደው የኮፕ-22 የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ የካርቦን ግብይት አሰራር ሥርዓት እንዲፈጠር ተሳትፎ ካደረጉ ሀገራት መካከል ኢትዮጵያ አንዷ መሆኗን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያ ብሔራዊ የካርቦን ገበያ ስትራቴጂ እያዘጋጀች መሆኗን አድንቀው ለተግባራዊነቱ በዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ፖሊሲና ማማከር አገልግሎት በኩል የገንዘብ እና የቴክኒክ ድጋፍ እንደሚያርጉ ገልጸዋል። ስትራቴጂው በፓሪስ የአየር ንብረት ስምምነት መሰረት የሀገሪቱን ዕምቅ አቅም ለመጠቀም እንደሚያግዝም ነው የጠቆሙት። በታዳሽ የኃይል አማራጭ ላይ የሚሰሩ የልማት ስራዎች ለዜጎች ጤናማ ከባቢ በመፍጠርር የማይተካ ሚና እንደሚኖረውም አስገንዝብዋል።
የአየር ትንበያ አገልግሎትን ይበልጥ ተደራሽና ዘመናዊ ለማድረግ የሚያግዙ ተግባራት በመከናወን ላይ ይገኛሉ
Feb 9, 2025 159
ሮቤ፤ የካቲት 2/2017(ኢዜአ)፡- የአየር ትንበያ አገልግሎትን ይበልጥ ተደራሽና ዘመናዊ ለማድረግ የሚያግዙ ተግባራት በመከናወን ላይ እንደሚገኙ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ጣቢያዎችን ማስፋትና ማዘመን ላይ ትኩረት ያደረገ ዐውደ ጥናት በባሌ ሮቤ ተካሂዷል። በኢንስቲትዩቱ የዳታና ክላይማቶሎጂ ዳይሬክተር አቶ መለሰ ለማ በወቅቱ እንዳመለከቱት፤ ኢንስቲትዩቱ የአየር ትንበያ አገልግሎትን ይበልጥ ተደራሽና ዘመናዊ ለማድረግ ትኩረት ሰጥቶ እየተንቀሳቀሰ ነው። በአሁኑ ወቅትም ከዓለም አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎትና ሌሎች ተቋማት በተገኘ የበጀት ድጋፍ አገልግሎቱን የማስፋትና የማዘመን ተግባራት እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም 16 አዳዲስ የምድርና የአየር ላይ የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ጣቢያዎችን ለመስራት የሚያስችሉ ቅድመ ሁኔታዎች በመመቻቸት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የደቡብ ኦሮሚያ ሚቲዎሎጂ አገልግሎት ማዕከል ዳይሬክተር አቶ ሙላቱ ወርቅነህ በበኩላቸው ፤ ማዕከሉ የአየር ትንበያ መረጃዎችን ለተጠቃሚዎች በየጊዜው እያደረሰ መሆኑን ተናግረዋል። የሚቲዎሮዎሎጂ አገልግሎቶችን ይበልጥ ማስፋትና ማዘመን ከዕውነታ ጋር የተቀራረባ የአየር ትንበያ አገልግሎት ለመስጠት እንደሚያግዝ አመልክተዋል። አቶ ሙላቱ እንዳሉ፤ ማዕከሉ በደቡብ ኦሮሚያ አካባቢዎች በቀጣይ የበልግ ወቅት 35 በመቶ ከመደበኛ በላይ፣ 40 በመቶ መደበኛና 25 በመቶ ከመደበኛ በታች እንደሚሆን ተተንብየዋል። ባለድርሻ አካላትም በተለይ ከመደበኛ በታች እንደሚያገኙ የተተነበዩ አካባቢዎች አርሶ አደሮች ማሳቸውን ፈጥነው በሚደርሱ የሰብል ዓይነቶች እንዲያለሙ ድጋፍና ክትትል እንዲያደርጉ መክሯል። በመድረኩ ላይ ከተሳተፉ ባለድርሻ አካላት መካከል የባሌ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሰለሞን ዳዲ፤ ከአገልግሎቱ በየወቅቱ የሚገኘው የአየር ትንበያ መረጃ መልካም አጋጣሚዎችን ለመጠቀምና ሊደርስ የሚችለውን አደጋ ደግሞ ለመቀነስ እንደሚያግዝ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የደቡብ ኦሮሚያ ሜትሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል ከሚሸፍናቸው አካባቢዎች መካከል ሁለቱ ባሌዎች፣ ቦረና ፣ጉጂ ፣ ከፊል አርሲና ምዕራብ አርሲ ዞኖች እንደሚገኙበት ተመልክቷል።
መገናኛ ብዙሃን የአየር ንብረት ለውጥን በተመለከተ የማህበረሰቡን ግንዛቤ የሚያሳድጉ ይዘቶችን ማጠናከር አለባቸው - የፕላንና ልማት ሚኒስቴር
Feb 8, 2025 110
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- መገናኛ ብዙሃን የአየር ንብረት ለውጥን በተመለከተ የማህበረሰቡን ግንዛቤ የሚያሳድጉ ይዘቶችን ማጠናከር እንዳለባቸው የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ተጨባጭ ተግባራትን እያከናወነች እንዳለችም ተጠቅሷል። ሚኒስቴሩ በተቀናጀ የመሬት አጠቃቀም ዕቅድ እና አስተዳደር፣ ዘላቂ የቡና ሃብት ልማት፣ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የደን ሀብትና የስነ-ህይወት ጥበቃ ላይ ለመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች በቢሾፍቱ ስልጠና እየሰጠ ነው። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በፖሊሲ የተደገፉ ተግባራትን እያከናወነች ትገኛለች። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው ብለዋል። በበጋ ወራትም የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ እና የተፋሰስ ልማትም ማህበረሰቡን በማሳተፍ በስፋት እየተተገበረ መሆኑን አንስተዋል። ይህም የተራቆቱ አካባቢዎች መልሰው እንዲያገግሙ በማድረግና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል የተፈጥሮ ሚዛን እንዲስተካከል እየተሰራ ይገኛል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ የበካይ ጋዝ ልቀትን ለመቀነስ ለታዳሽ ኃይል ልማት ትኩረት መስጠቷንም ነው ሚኒስትር ዴኤታው ያብራሩት። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖው ድንበር ዘለል በመሆኑ የመከላከል ስራውም ዓለም አቀፋዊ ትብብርን ይሻል ብለዋል። መገናኛ ብዙሃን የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እየተሰሩ ያሉ ስራዎች ላይ በቂ ግንዛቤ በመያዝ በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባም አንስተዋል። በዚህም በተጨባጭ መረጃዎች ላይ በመመስረት የማህበረሰቡን ግንዛቤ ለሚያሳድጉ ይዘቶች ትኩረት እንዲሰጡ ጠይቀዋል።
በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የለሙ ተፋሰሶች ምርታማነታችንን በመጨመር ተጠቃሚ ሆነናል - አርሶ አደሮች
Feb 8, 2025 86
ደብረ ማርቆስ/ደብረብርሃን ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡ - በአካባቢያቸው ባለፉት ዓመታት በተከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የለሙ ተፋሰሶች ምርታማነታቸውን በመጨመር ተጠቃሚ መሆናቸውን በምስራቅ ጎጃምና ሰሜን ሸዋ ዞኖች አርሶ አደሮች ገለጹ። በሁለቱ ዞኖች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ዘንድሮም ተጠናክሮ በመቀጠል ከ69 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ የተጎዳ መሬትን ለማልማት ወደ ተግባር መገባቱን የየዞኖቹ ግብርና መምሪያዎች አመላክተዋል። በምስራቅ ጎጃም ዞን የደጀን ወረዳ የሹምብሪ ቀበሌ አርሶ አደር ምህረቱ ሲሳይ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት፤ የተፈጥሮ ሃብት ልማቱ ተጎድቶ የነበረው አካባቢያቸው እንዲያገግም በማድረግ ማሳቸው ከጎርፍ እንዲጠበቅ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። የማሳቸው ለምነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ በሄክታር ከአራት ኩንታል በላይ ጭማሪ ያለው ምርት እንዲያገኙ በማስቻል ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ገልጸዋል። በተጨማሪም ደርቀው የነበሩ ምንጮችና ሌሎች የውሃ መገኛ ቦታዎች እንደገና ውሃ በማመንጨታቸው በመስኖ ልማት በመሰማራት ተጨማሪ ምርት እያገኙ መሆኑንም ጠቅሰዋል። እያገኙት ያለውን ጥቅም ለማስፋትም ዘንድሮ በሚካሄደው የተፈጥሮ ሃብት ስራ በቁርጠኝነት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በአዋበል ወረዳ የጭፍር ቀበሌ አርሶ አደር ደስ ይበለው ጌጡ በበኩላቸው፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው የማሳቸው የአፈር ለምነት እንዲጨምር ማስቻሉን አስታውቀዋል። የተራቆተ መሬታቸው ከአራት ዓመት ወዲህ በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እንዲያገግም በማድረግ ስንዴ፣ ጤፍና ባቄላ ከራሳቸው አልፎ ለገበያ እያመረቱ መሆኑን ገልጸዋል። የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና ልማት ስራው በእንስሳት ሃብት ልማት በመሰማራት ተጨማሪ ሃብት እንዲያፈሩ እንዳስቻላቸው የተናገሩት ደግሞ በእነማይ ወረዳ የወይራ ቀበሌ አርሶአደር የግዛው አለምሰገድ ናቸው። ከማሳቸው በተጓዳኝ የእንስሳት መኖ በማልማት የስጋ ከብቶችን እያደለቡ በመሸጥ በዓመት እስከ 80ሺህ ብር ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መሆኑን አብራርተዋል። በተመሳሳይ በሰሜን ሸዋ ዞን የአንጎለላ ጠራ ወረዳ አርሶ አደር ገብርየ ነጋሽ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት የተራቆቱ ተራራማ ቦታዎችን በማልማት ተጠቃሚ ሆነዋል። በዚህም አንድ ሄክታር ተኩል መሬት ላይ ዛፍ በመትከል ከአጣና ሽያጭ 160 ሺህ ብር ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። የአፈና ውሃ ጥበቃ ስራው የአካባቢውን የአፈር መከላት በመከላከሉም በሰብል ምርት ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን አስረድተዋል። ሌላው አርሶ አደር ደርቤ ጌታነህ ፤ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራው ተራቁቶ የቆየውን መሬት መልሶ እንዲያገግም ማስቻሉን ገልጸዋል። ቀደም ሲል በሰሯቸው የማሳና የጋራ ላይ እርከኖች የእርሻ መሬታቸው ለም መሬት በጎርፍ ከመወሰድ በመታደግ ለሰብል ምርት ማደግ እንዳገዛቸው ተናግረዋል። የበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ያስገኘላቸውን ጠቀሜታ ለማስቀጠልም በዚህ የበጋ ወራት በልማቱ ስራ እየተሳተፉ እንደሚገኙ አመልክተዋል። በምስራቅ ጎጃም ዞን የግብርና መምሪያ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ባለሙያ አቶ ታደሰ በቀለ እንደገለጹት፤ አርሶ አደሩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራን የህልውና ጉዳይ አድርጎ እየተገበረው ይገኛል። ዘንድሮ ከ45ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ለማልማት ታቅዶ ከጥር 15/2017 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ተግባር መገባቱን አመልክተው፤ በስራውም አርሶ አደሮች እየተሳተፉ መሆኑን አብራርተዋል። በዞኑ ባለፈው ዓመት 21ሺህ 700 ሄክታር መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መከናወኑን ተመልክቷል። ይህ በእንዲህ እንዳለ በሰሜን ሸዋ ዞን ግብርና መምሪያ የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ጌታነህ ተክለማሪያም በበኩላቸው፤ በዚህ የበጋ ወራት በ15 አዲስ ተፋሰሶች 24 ሺህ 385 ሄክታር መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ጊዜያት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአካባቢውን ስነ ምህዳር ከመጠበቅ ባለፈ የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ተናግረዋል። በከተማው ዙሪያ ባሉ የገጠር ቀበሌዎች በ1 ሺህ 200 ሄክታር መሬት ላይ ተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተካሄደ ነው ያሉት የደብረ ብርሀን ከተማ አስተዳደር ግብርና መምሪያ ሀላፊ አቶ መርሻ አይሳነው ናቸው።
በጋምቤላ ክልል የሙቀት መጠን እየጨመረ በመምጣቱ የመንግስት የስራ ሰዓት ላይ ማሻሻያ ተደረገ
Feb 7, 2025 89
ጋምቤላ፤ ጥር 30/2017(ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል የሙቀት መጠን እየጨመረ በመምጣቱ የመንግስት የስራ ሰዓት ላይ ማሻሻያ መደረጉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድርና ካቢኔ ጉዳዮች ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ኡቶው ኡኮት ዛሬ እንደገለጹት የሙቀቱ መጠን እየጨመረ በመምጣቱና ለስራ ምቹ ባለመሆኑ ከነገ የካቲት 1 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ለሶስት ወራት የሚቆይ የመንግስት የስራ ሰዓት ለውጥ ተደርጓል። በለውጡ መሰረትም ቀደም ሲል ከጧቱ አንድ ሰዓት እስከ ስድስት ሰዓት ተኩል የነበረው ከአንድ ሰዓት እስከ አምስት ሰዓት ተኩል እንዲሆን ተወስኗል። እንዲሁም ከሰዓት በኋላ ከዘጠኝ ሰዓት እስከ አስራ አንድ ሰዓት ተኩል የነበረው ከአስር ሰዓት እስከ አስራ ሁለት ሰዓት ተኩል እንዲሆን ተወስኗል ብለዋል። የስራ ሰዓት ለውጡ ወይናደጋ የአየር ንብረት ያላቸውን የመንገሺና የጎደሬ ወረዳዎችን እንደማይጨምር የገለጹት ኃላፊው፤ የክልሉ የመንግስት ሰራተኞች በተጠቀሰው የተለመደውን ስራቸውን እንዲያከናውኑ ጥሪ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የጋምቤላ ክልል የሚትዎሮሎጂ አገልግሎት መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ ተስፋሁን ዓለሙ በበኩላቸው በአሁኑ ወቅት የክልሉ አማካይ የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን 39 ነጥብ 2 ዲግሪ ሴልሸስ መሆኑን ተናግረዋል። እንዲሁም የሌሊቱ ዝቅተኛ የሙቀት መጠን ደግሞ 23 ዲግሪ ሴልሸስ መድረሱን ጠቁመው፤ የሙቀቱ መጠን በቀጣዮቹ ሶስት ወራት አሁን ካለው ሊጨምር እንደሚችልም አመላክተዋል። ባለፉት ወራት የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን 35 ዲግሪ ሴልሸስ፤ የሌሊቱ ደግሞ ከ21 ዲግሪ ሴልሸስ በታች እንደነበር አቶ ተስፋሁን ገልጸዋል።
ምክር ቤቱ የአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነትን ለመከላከል የሚያግዝ ረቂቅ አዋጅ አፀደቀ
Feb 7, 2025 91
አዲስ አበባ፤ ጥር 30/2017(ኢዜአ)፡- የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአካባቢና ማህበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ ተጋላጭነትን ለመከላከል የሚያግዝ ረቂቅ አዋጅ መርምሮ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡ ምክር ቤቱ 18ኛ መደበኛ ስብሰባውን አድርጓል። በስብሰባው ላይ የምክር ቤቱ የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢ እና አካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሪት ፈቲያ አህመድ የአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነትን ለመከላከል የሚያግዝ ረቂቅ አዋጅን አስመልክቶ ሪፖርት እና የውሳኔ ሀሳብ አቅርበዋል። ሰብሳቢዋ አዋጁ በማደግ ላይ የሚገኘውን የኢኮኖሚ ዕድገት በአካባቢና ተፈጥሮ ሀብት ላይ ጉልህ ጉዳት የማያስከትልና ለአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነት የማይበገር እንዲሆን የሚያስችል ሥርዓትን ለመዘርጋት እንደሚያግዝ ገልጸዋል። አዋጁ ኢትዮጵያ ከተቀበለቻቸው ዓለም አቀፍ የአካባቢና አየር ንብረት ለውጥ ስምምነቶችና ሕግጋት ጋር የሚጣጣም የሕግ ማዕቀፍ ያለው መሆኑን ተናግረዋል። የምክር ቤቱ አባላት በበኩላቸው፤ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም መገንባት ዘላቂ ልማት እና የህብረተሰብ ተሳትፎን ለማሳደግ ለሀገር ዕድገት ጉልህ ሚና እንደሚኖረውና በዚህ ረገድም ረቂቅ አዋጁ አጋዥ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። ምክር ቤቱ የአካባቢና ማህበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ ረቂቅ አዋጁን በመመርመር በሙሉ ድምጽ ማጽደቁን ከምክር ቤቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በክልሉ በተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ መልሶ ያገገመ 229 ሺህ ሄክታር መሬት ለማህበረሰቡ ተላልፏል - የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ
Feb 7, 2025 99
መቀሌ፤ ጥር 30/2017(ኢዜአ)፡- በትግራይ ክልል በተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ መልሶ ያገገመ 229 ሺህ ሄክታር መሬት ለተደራጁ አርሶ አደሮች መተላለፉን የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ገለፀ። በቢሮው የተፋሰስ ልማት ቡድን መሪ አቶ ጠዓመ ገብረስላሴ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በክልሉ በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ ምክንያት የተጎዱ መሬቶች በተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ መልሰው እንዲያገግሙ ለማድረግ እየተሰራ ነው። በዚህም ቀደም ሲል በተለያዩ ተፋሰሶች በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የለማ 229 ሺህ ሄክታር መሬት በማህበር ለተደራጁ 198 ሺህ አርሶ አደሮች እንዲሰጥ መደረጉን ገልጸዋል። የለሙ ተፋሰሶችን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ነፃ በማድረግ ለአርሶ አደሩ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማዋል እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። አርሶ አደሮች የለሙ ተፋሰሶችን በመንከባከብ በቋሚነት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ህጋዊ የባለቤትነት ማረጋገጫ ካርታ እንዲሰጣቸው መደረጉንም አቶ ጠዓመ አስረድተዋል። አርሶ አደሮቹ የለሙ ተፋሰሶቹን ከመንከባከብ ባለፈ በንብ ማነብና በእንስሳት መኖ ልማት ሥራ ተሰማርተዋል። ልማቱን ለማጠናከርም የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ለቁም እንስሳት መግዣ የሚሆን 194 ሚሊዮን ብር በተዘዋዋሪ ብድር ማቅረቡንም አቶ ጠዓመ ጠቁመዋል። ከልማቱ ተጠቃሚ አርሶ አደሮች መካከል በትግራይ ምስራቃዊ ዞን የሀውዜን ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ገብረአነንያ ታደሰ፣ ማህበራቸው አንድ ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ቦታ መረከቡን ገልፀዋል። የማህበሩ አባላት ከሁለት ሚሊዮን ብር በላይ መቆጠባቸውንና ከቁጠባ በብድር ባገኙት ገንዘብ የእርድ እንስሳት የማድለብ ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል። የአፅቢ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር መብርሂት አሰፋ በበኩላቸው ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በቅርቡ በመሰረቱት ማህበር አስር ሄክታር የሚሆን የለማ ተፋሰስ መረከባቸውን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በለማው ተፋሰስ የተለያዩ ቋሚ አትክልቶችን በመትከል ተጠቃሚ ለመሆን ተግተው እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በዞኑ በተፋሰስ ስራ በለሙ ስፍራዎች ላይ የሚተከሉ ችግኞች በስፋት እየተዘጋጀ ነው
Feb 6, 2025 101
ጎንደር፤ ጥር 29/2017(ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በዘንድሮ የበጋ ወቅት በተፋሰስ ስራዎች በለሙ ስፍራዎች የሚተከሉ ችግኞች በስፋት እየተዘጋጁ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ የመምሪው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ከዘጠኝ ሺህ በሚበልጡ የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች የአካባቢውን ስነ ምህዳር ለመጠበቅ የሚያግዝ አገር በቀል ችግኞች እየተዘጋጁ ነው። የተፋሰስ ልማት በተከናወነበት 24 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ እንደሚተከል ገልጸዋል። ባለፈው የክረምቱ ወራት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በህብረተሰቡ ተሳትፎ የተተከለው ችግኝ በአሁኑ ወቅት ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተከልሎ የጥብቃና ክብካቤ ስራ እየተከናወነ መሆኑንም ጠቁመው፤ ከ80 በመቶ በላይ ጽድቀት መጠን እንዳለ አውስተዋል፡፡ በለሙ ተፋሰሶች ላይ 384 ነባር ተፋሰሶች ጽህፈት ቤት ተቋቁመው በንብ ማነብ፣ በእንስሳት እርባታና ማድለብ ስራዎች ሰፊ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እያስገኙ መሆኑን ገልጸው፤ ከ18 ሺህ በላይ ለሚሆኑ የአርሶ አደሩ ልጆችም የስራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል። በተያዘው የበጋ ወራት በ815 ነባርና አዲስ ተፋሰሶች ላይ 24 ሺህ ሄክታር የሚሸፍን የእርከንና ክትር ስራዎች እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የጎንደር ዙሪያ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ አለባቸው ምህረት በበኩላቸው በዘንድሮ የበጋ ወራት ለሚከናወነው የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ በስነ ህይወታዊ ዘዴ ለመጠበቅ የችግን ማፍላት መጀመሩን ገልፀው፤ በመጪው ክረምት የሚተከል መሆኑን አብራርተዋል። በማዕከላዊ ጎንደር ዞን እስከ የካቲት አጋማሽ በሚዘልቀው የበጋ ወራት ከ440 ሺህ በላይ ህዝብ በአፈርና ውሃ እቀባ ስራው በንቅናቄ እየተሳተፈ እንደሚገኝ ተመልክቷል።
የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመላቀቅ የተፋሰስ ልማት ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል - ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ
Feb 5, 2025 91
ጋምቤላ፤ ጥር 28/2017 (ኢዜአ)፦ በክልሉ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመላቀቅ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። በክልሉ የ2017 የአፈርና ውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት የንቅናቄ መርሃ ግብር የክልሉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በተገኙበት በማጃንግ ዞን ጎደሬ ወረዳ ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ በቦታው ተገኝተው የአፈርና ውሃ ጥበቃ መርሃ ግብሩን ሲያስጀምሩ እንዳሉት፤ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ዓይነተኛ ድርሻ አላቸው። በተለይም የተራቆቱና የተጎዱ አካባቢዎች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በመጠናከር "የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመላቀቅ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ተግተን ልንሰራ ይገባል" ብለዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተፋሰስ ልማትና የአረንጓዴ አሻራ ስራዎች የአካባቢ መራቆትንና የአየር ንብርት ለውጥን በመከላከል በግብርናው ዘርፍ ውጤት እንዲመጣ አስችሏል ብለዋል። በመሆኑም እንደ ክልል የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ላይ ይበልጥ ተግቶ መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በዕለቱ ለተጀመረው የአፈርና ውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት ስራ ስኬታማነት በየደረጃው የሚገኙ የአመራር አካላት የህዝብ ንቅናቄን በመፍጠር ጠንክረው ሊሰሩ እንደሚገባም አሳስበዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ፓል ቱት በበኩላቸው እንዳሉት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር እርጥበታማነትንና ለምነትን በማሻሻል የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ የላቀ አበርክቶ አለው። በዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ሥራ በሁሉም ወረዳዎች ከ145 ሺህ ሄክታር የተራቆተ መሬት ለመሸፈን ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል። በዚህም በሁሉም ወረዳዎች በተለዩ 138 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እንደሚከናወንም አብራርተዋል። በዘንደሮው ዓመት የሚካሄደው የአፈርና ውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት ስራ ከቀዳሚው ዓመት ጋር ሲነፃፀር በእጥፍ ብልጫ ያለው መሆኑን ጠቁመዋል። የተፋሰስ ልማት የንቅናቄ መርሃ ግብር ከ40 ሺህ በላይ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለማሳተፍ ግብ መቀመጡንም አቶ ፓል ገልጸዋል።
ሐይቆችን ከእምቦጭ አረም የመታደግ ጥረቱ ምን ደረጃ ላይ ይገኛል?
Feb 5, 2025 98
በኢትዮጵያ አይነተ ብዙ መጤ የዕጽዋት ዝርያዎች በውሃ አካላት፣ በእርሻና በግጦሽ መሬት ላይ በፍጥነት እየተዛመቱ መልከ ብዙ አደጋ እያስከተሉ ነው። በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ መጤ አረሞች በውሃማ አካላት ላይ እየተስፋፉ በመምጣታቸው በብዝሐ ሕይወት ላይ የሕልውና ስጋት ደቅነዋል። በግዙፉ የጣና ሐይቅ ጨምሮ በውሃማ አካላት ብዝሐ ሕይወት አደጋ ከደቀኑ መጤ አረሞች መካከል እምቦጭ ትልቁን ድርሻ ይዟል። እምቦጭ የውሃ መጠን በመቀነስ፣ የዕጽዋትና የእንስሳት ብዝሃ ሕይወት በማመናመን ካለው ከፍተኛ ስጋት አኳያ ባለፉት ዓመታት ስጋቱን ለመቀልበስ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ባለድርሻ አካላት ጥረት አድርገዋል። ክልሎች በየውሃማ አካላቱ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም ለመከላከል በሰው ጉልበት እና በሜካኒካል መንገዶች ጥረት ሲያደርጉ ይስተዋላል። ኢዜአ እምቦጭን ጨምሮ በፍጥነት እየተዛመቱ የሚገኙ የብዝሐ ሕይወት አደጋ የሆኑ የደቀኑ አረሞችን ለመከላከል ሲደረጉ የነበሩ ጥረቶች ምን ላይ እንዳሉ በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የስራ ኃላፊዎችን አነጋግሯል። በአማራ ክልል አካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን የአካባቢና አየር ንብረት ለውጥ ዳይሬክተር አወቀ ይታይ፤ በክልሉ ጣና ሃይቅን የወረረውን የእንቦጭ አረም ለማስወገድ በዘመቻ መልክ ሲሰሩ የነበሩ ስራዎች አስታውሰዋል። የጣና ሐይቅ የእምቦጭ አረም በዘላቂነት ለመፍታት የክልሉ መንግስት ብቻ ሳይሆን የሁሉንም ባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት እንደሚሻ ገልጸዋል። ከዚህ በፈት የእምቦጭ ጉዳይ አጀንዳ በማድረግ ችግሩን ለመቀልበስ ጥሩ እንቅስቃሴ እንደነበር አስታውሰው፤ አሁን ግን በወቅታዊ ሁኔታዎች ሳቢያ መቀዛቀዝ እንዳለ አንስተዋል። በዚህም የእምቦጭን ጉዳይ አጀንዳ አድርጎ ዳግም በማነቃነቅ አሁናዊ መቀዛቁዙን ለመቅረፍ ጥረት እንደሚደረግ አረጋግጠዋል። በኦሮሚያ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የብዝሃ ሕይወት ጥበቃና እንክብካቤ ዳይሬክተር ብርሃኑ ኢደቲ እንዳሉት ደግሞ በክልሉ የተከሰቱ መጤ አረሞችን ለመከላከልና መቆጣጠር በልዩ ትኩረት ሲሰራ ቆይቷል። እምቦጭን ጨምሮ መጤ አረሞችን ለለመቀነስ ህብረተሰቡ፣ መንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት በትብብር መስራታቸውን ገልፀዋል። በዚህም በባቱ ደንበል ሐይቅ ላይ ተከስቶ የነበረውን የእምቦጭ አረም መቀነስ መቻሉን ጠቅሰዋል። ይሁንና አሁንም ቢሆን ከችግሩ ስፋት አኳያ ተቋማዊ የሆነ ተከታታይነት ያለው ቅንጅታዊ አሰራርን ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ብዝሃ ህይወት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር መለሰ ማርዮ(ዶ/ር) እምቦጭና ሌሎች መጤ የዕጽዋት ዝርያዎችን የመከላከል ጥረት የአንድ ሰሞን ዘመቻ መሆን እንደሌለበት ያምናሉ። አረሞቹ ማጥፋት አዳጋች እንደሆነ የገለጹት ዶክተር መለሰ፤ አሉታዊ ተጽዕኖውን ግን መቀነስና መቆጣጠር እንደሚቻል ተናግረዋል። በመሆኑም በአካባቢና ብዝሃ ሕይወት ላይ ከሚያስከትሉት ከፍተኛ ጉዳት አኳያ አረሞችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የተቋማት ቅንጅታዊ አሰራር ማጠናከር እና የጋራ አደረጃጀት መፍጠር እንደሚገባ ነው ያነሱት። ይህ ደግሞ ከፍተኛ የፋይናንስ አቅም የሚጠቅይቅ በመሆኑ ከተለያዩ ምንጮች ፋይናንስ በማፈላለግ እንዲሁም የህብረተሰቡን አቅም በመጠቀም የተቀናጀ ጥረት ማድረግ እንደሚጠይቅ አስረድተዋል።
ፓርኩን ከእሳትና ሌሎች ሰው ሰራሽ አደጋዎች ለመከላከል የሚያግዙ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Feb 5, 2025 108
ሮቤ፤ ጥር 28/2017(ኢዜአ)፡- የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን ከእሳትና ሌሎች ሰው ሰራሽ አደጋዎች መከላከል የሚያስችሉ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆናቸውን የፓርኩ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የፓርኩ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሻሚል ከድር ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ፓርኩን ከእሳትና ሌሎች ሰው ሰራሽ አደጋዎች መከላከል የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በፓርኩ ላይ ተጽዕኖ ከሚያሳድሩ ሰው ሰራሽ አደጋዎች መካከል ሰደድ እሳት፣ ህገ-ወጥ ሰፈራና ልቅ ግጦሾ ዋና ዋናዎቹ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይ የበጋው ሞቃታማ አየር ለእሳት አደጋ መቀስቀስ ምቹ ሁኔታ ስለሚፈጥር ህብረተሰቡንና አጋር አካላትን በማሳተፍ የቅድመ ጥንቃቄ ሥራዎች በመከናወን ላይ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በፓርኩ ክልል ባለፉት አራት ዓመታት የእሳት አደጋ አለመከሰቱን የጠቆሙት ኃላፊው በአሁኑ ወቅትም ህብረተሰቡን ያሳተፈ የቁጥጥርና የክትትል ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ የፓርኩ አዋሳኝ በሆኑ ዲንሾ፣ ጎባ፣ አዳባና ሌሎች አዋሳኝ ወረዳዎች ውስጥ በየደረጃው ካሉ አመራር አባላትና የህብረተሰብ ተወካዮች ጋር የአደጋ ቅድመ መከላከል የመግባቢያ ሰነድ መፈራረማቻውን አስረድተዋል። እንዲሁም የእሳት አደጋ ስጋት ናቸው ተብለው በጥናት በተለዩ የፓርኩ የተለያዩ ቦታዎችም በእሳት አደጋ መከላከል ሙያ የሰለጠኑ 192 አባላት ያላቸው 16 የእሳት አደጋ ተከላካይ ብርጌድ መቋቋማቸውን ተናግረዋል። ለብርጌድ አባላቱ አልባሳት፣ ትጥቅና የእሳት ማጥፊያ መሳሪያዎች ማሟለት የሚያስችሉ ቅድመ ሁኔታዎች በመመቻቸት ላይ መሆኑንም ጠቁመዋል። ለእሳት አደጋ ቅድመ ጥንቃቄ ተግባራት በየደረጃው ከሚገኙ የመስተዳድር አካላትና በጎ አድራጊ ድርጅቶች በበጀትና በስልጠና ድጋፍ እያደረጉ መሆናቸውንም አመልክተዋል። ፓርኩ በዓለም ቅርስነት ሲመዘገብ ሊሟሉ የሚገቡ ቅድመ ሁኔታዎችን መሰረት ያደረገ መሆኑን በመገንዘብ ፓርኩን ከአደጋ ስጋት ነፃ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ነው አቶ ሻሚል የተናገሩት። የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ከ2 ሺህ ስኩዌሬ ካሬ ሜትር በላይ መሬት የሚያካልል ሲሆን በውስጡም የደጋ አጋዘን፣ ጦጣ፣ ፍልፈልን ጨምሮ ሌሎች አያሌ የዕጽዋትና አዕዋፍ መገኛ መሆኑን የፓርኩ ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል። የተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም(ዩኔስኮ) በ45ኛው የአለም የቅርስ ጉባኤ ላይ ፓርኩን በቋሚ ቅርስነት መመዝገቡ ይታወሳል።
ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት ለምታደርገው ጥረት ድጋፋችን ይቀጥላል - የልማት አጋር ሀገራትና ድርጅቶች
Feb 4, 2025 112
አዲስ አበባ፤ ጥር 27/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት በምታደርገው ጥረት ድጋፋቸው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የልማት አጋር ሀገራትና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ገለጹ። በኮፕ-29 ጉባኤ ቃል በተገቡ ሥራዎች ትግበራ፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ስኬትና የቀጣይ መርሃ ግብሮችን አስመልክቶ በአዲስ አበባ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት የልማት ድርጅት ተወካይ ሳሙኤል ዶ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የምታደርገው ስኬታማ ጥረት ዓለም አቀፍ ተደማጭነቷን የሚያሳድግ መሆኑን ተናግረዋል። የተጀመሩ ስራዎችን ለማጠናከር፣ ዕድሎችን በአግባቡ ለመጠቀም እና ለችግሮች የተቀናጀ ምላሽ ለመስጠት የልማት አጋር ድርጅቶች ሚና ወሳኝ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ የአየር ንብረት እና የግብርና መሪ ኒና ሂሰን(ዶ/ር)፤ እንግሊዝ በአፍሪካ ሀገራት በአየር ንብረትና ተፈጥሮ ጥበቃ ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየሰራች መሆኑን ገልጸዋል። በፎረሙ የሚቀርቡ ሃሳቦችም ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት በምታደርገው ጥረት የሀገራቱን ትብብር ለማጠናከር እንደሚረዳ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የኖርዌይ ኤምባሲ የአየር ንብረት ለውጥ አማካሪ ሰለሞን ዘውዴ(ዶ/ር)፤ ሁለቱ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ የትብብር ስምምነት መፈራረማቸውን አስታውሰዋል። በዚህም በካርቦን ሽያጭና ደን ልማት ዘርፍ የሀገራቱን ትብብር ለማጠናከር በቅርበት እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአካበቢና የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት ስትራቴጂክ አጋርነት መሪ ሥራ አስፈፃሚ መንሡር ደሴ፤ ኢትዮጵያ የተቀበለቻቸውን ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ መከላከል ስምምነቶች እየተገበረች ነው ብለዋል። ለዚህም ፖሊሲና ስትራቴጂ ቀርጻ ውጤታማ ስራዎች በማከናወን ላይ መሆኗን አንስተዋል። በቀጣይ በብራዚል በሚካሄደው የኮፕ-30 ጉባኤም የኢትዮጵያንና አፍሪካን ጥቅም ማስጠበቅ የሚያስችሉ የትኩረት መስኮችን ለአጋር አካላት የማስተዋወቅ ስራ እየተከናወነ አንደሚገኝ አስረድተዋል። በዛሬው የምክክር መድረክ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመዋጋት ተግባራዊ ያደረገቻቸውን ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎችና የተገኙ ውጤቶችን ለልማት አጋሮች ግንዛቤ መፈጠሩን ገልጸዋል። በዚህም የልማት አጋር ሀገራትና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ለኢትዮጵያ እያደረጉት ያለው ድጋፍ ውጤት እያመጣ መሆኑን በማሳወቅ ድጋፋቸው ተጠናክሮ እንዲቀጥል መግባባት የተፈጠረበት ነው ብለዋል።
በደቡብ ኦሞ ዞን የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ ነው
Feb 4, 2025 142
በናፀማይ፤ ጥር 27/2017(ኢዜአ)፡-በደቡብ ኦሞ ዞን የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ በዘንድሮ ዓመት በዞኑ ከ125 ሺህ በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ ከ35 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት ታቅዶ እየተሰራ ነው። በልማቱ ከሚከናወኑ የአፈርና ውሃ ልማትና ጥበቃ ሥራዎች በተጨማሪ የግጦሽ ሣር ከለላ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በንቅናቄ እየተካሄደ ባለው የልማት ሥራ 47 ንዑስ ተፋሰሶች እንደሚለሙ ገልጸው፣ ከተፋሰስ ሥራው ጎን ለጎን በ2 ሺህ 319 ሄክታር መሬት ላይ የለማ የግጦሽ ሣር ከለላና የእንክብካቤ ሥራዎች ይከናወናሉ ብለዋል። እንደ ኃላፊው ገለጻ በዞኑ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጣቸው ተራራማ በሆኑ ማሌ፣ በናፀማይ እና ሳላማጎ ወረዳዎች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች በስፋት ይከናወናሉ። መልክአ ምድራዊ አቀማመጣቸው ዝቅተኛ በሆኑ እንደ ሐመር፣ ዳሰነች እና ኛንጋቶም ባሉ አካባቢዎች ደግሞ የግጦሽ ሣር ከለላ፣ የብዝሃ ሕይወት ጥበቃና እንክብካቤ ሥራዎች ትኩረት እንደተሰጣቸው አስታውቀዋል። በዞኑ በናፀማይ ወረዳ ይርጋ ቀበሌ እየተከናወነ ባለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ላይ የተሳተፉት የቀበሌው ነዋሪዎች ቀደም ሲል በተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የተለያየ ጥቅም ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ጎርፍና መሰል የተፈጥሮ አደጋዎችን ከመከላከል አንስቶ ለግብርና ምርታማነት ማደግ አስተዋጾ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል አርብቶ አደር ከፍያለው ጽጌ እንደገለጹት፣ ከዚህ ቀደም በቀበሌው ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ፣ የአፈር መሸርሸር እና የመሬት ለምነት ማጣት ችግሮች እንደነበሩ አስታውሰዋል። በቀበሌው በተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች ከቅርብ ዓመታው ወዲህ እነዚህ ችግሮች እየተፈቱ መምጣታቸውን ጠቁመዋል። ለዚህም በአካባቢያቸው የተራቆቱና የተጎዱ አካባቢዎች በማገገማቸው ለእርሻ ሥራ መዋል እንደጀመሩና የደረቁ ምንጮችም መልሰው መጎልበታቸውን ተናግረዋል። የተፋሰስ ልማት ውጤታማነትን አጠናክሮ ለማስቀጠልም ዘንድሮም የልማት ሥራውን አጠናክረን ቀጥለናል ሲሉ ተናግረዋል። "አካባቢያችን ተዳፋት በመሆኑ በየጊዜው በጎርፍ አደጋ ምክንያት ማሳችን ምርት መስጠት አልቻለም ነበር" ያሉት ደግሞ ሌላዋ የቀበሌው ነዋሪ ወይዘሮ እቴቴ ፅጌ ናቸው። ባለፉት ሦስት ዓመታት በአካባቢው በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የተጎዱ የእርሻ ማሳዎች መልሰው በማገገም ምርት መስጠት መጀመራቸውን ገልጸዋል። ተፋሰስ በተሰራባቸው አካባቢዎች ለእንስሳት የሚሆን ሣር ማልማታቸውንና ይህም ተጨማሪ የመኖ አማራጭ እንደፈጠረላቸው ጠቅሰው፣ ተጠቃሚነታቸውን ለማጠናከር የለማውን ሣር የማካለል ሥራ እያከናወኑ መሆናቸውን ተናግረዋል። በወረዳው በንቅናቄ በሚካሄደው የተፋሰስ ልማት 10 ሄክታር መሬት ለማልማት እና የግጦሽ ሳር ከለላ ለማካሄድ ወደ ስራ መገባቱን የተናገሩት የበናፀማይ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ክላሽ አንግሪ ናቸው። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች በአካባቢው በታየው ተጨባጭ ለውጥ የአካባቢው ማህበረሰብ ተሳትፎ እያደገ መምጣቱን ተናግረው፣ ዘንድሮም ልማቱን ለማጠናከር የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል። ለአንድ ወር በህዝብ ንቅናቄ በሚከናወነው በዚሁ ሥራ የተለያዩ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውንም አስረድተዋል። "የአፈር ሀብታችን ለብልፅግናችን" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ያለው የዘንድሮ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ሁሉም አካባቢዎች ከጥር 15 ጀምሮ ተጠናክሮ መቀጠሉ ታውቋል።
ባለፉት ዓመታት ያከናወናቸው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራዎች የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ አስችሏል-አርሶ አደሮች
Feb 4, 2025 93
መቱ፤ጥር 27/2017 (ኢዜአ)፦ባለፉት ዓመታት ባከናወኗቸው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ አስችሏል ሲሉ የኢሉአባቦር ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ። ቀድሞ የአፈርና ውሃ ጠበቃ ስራ በበጋ ወቅት ብቻ ያከናውኑ የነበረ ሲሆን አሁን ላይ መደበኛ ስራቸው አድርገው መተግበር መጀመራቸውንም ገልጸዋል። በኢሉአባቦር ዞን የበቾ ወረዳ በኮጂ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር አብዱ ሱጳ፤ ለሰብል ምርት ይጠቀሙበት የነበረው ማሳቸው ተዳፋታማ በመሆኑ በጎርፍ ታጥቦ ለምነቱን አጥቶ እንደነበር ያስታውሳሉ። ከዚህም የተነሳ ማሳውን ማረስ አቁመው እንደነበርና ሰብል የማምረትና ቤተሰባቸውን የማስተዳደር አቅማቸው ላይ ችግር ፈጥሮባቸው እንደነበር ተናግረዋል። የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በአካባቢያቸው ሲጀመር ከግብርና ባለሙያዎች ባገኙት ምክር ማሳቸው ላይ እርከን መስራታቸውንና የተለያዩ ዛፎችንና አትክልቶችን መትከል እንደጀመሩ ገልጸዋል። ወደ ሁለት ሔክታር መሬታቸው ላይ ባከናወኑት የተፋሰስ ልማት ስራ ቦታው መልሶ ማገገሙንና በአጭር ጊዜ ሙሉ በሙሉ ወደ አረንጓዴነት መለወጡንም ገልጸዋል። አቶ አብዱ፥ ባገገመ መሬታቸው ላይ ሙዝ፣ አቮካዶ፣ ፓፓያን እንዲሁም የተለያዩ መኖ ዓይነቶችን እያለሙ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም ቡናና ኮረሪማን የመሰሉ የገቢ ምንጭ የሚሆኑ ተክሎችንም የተከሉ ሲሆን በዚያው ስፍራ 50 ዘመናዊ የንብ ቀፎዎችም በማስቀመጥ በዓመት እስከ 500 ኪሎ ግራም ማር ለማግኘት ማቀዳቸውንም አብራርተዋል። የከብት መኖውን ለከብቶቻቸው ከመመገብ ባለፈ አጭደው ለሌሎች በመሸጥ ገቢ እያገኙ ሲሆን ከንብ ማነብ ስራውም ትልቅ ገቢ እንደሚያገኙ ተስፋ አድረገዋል። ሌላው የአካባቢው ነዋሪ አቶ እንግዳ ሹባ፥የተፋሰስ ልማት ስራው ተጠቃሚ ሊያደርጋቸው የሚችል መልካም ነገር ይዞላቸው መምጣቱን ገልጸዋል። እርሳቸውም በማሳቸው ላይ በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ መሬቱ ተመልሶ ማገገሙን ተከትሎ የተለያዩ አትክልትና ፍራፍሬዎችን እያለሙ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በዚህም በቀጣዮቹ ዓመታት ጥሩ የገቢ ምንጭ እንደሚሆናቸው ተስፋ ማድረጋቸውን ነው የተናገሩት። በዞኑ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጠበቃ ስራ የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ በማድረግ አርሶ አደሩንም በኢኮኖሚ ተጠቃሚ የሚያደርጉ ውጤቶች እየተገኙ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የኢሉአባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ምክትል ኃላፊ አቶ መልካሙ ጫሊ ናቸው። በተሰራው ስራ የዞኑን የደን ሽፋን መጨመር መቻሉን ጨምሮ የተፈጥሮ ሚዛንን መጠበቅ፣የአፈር እጥበትና መሸርሸርን መከላከል፣ በበጋው ወቅት ከብቶች በመኖ አጥረት እንዳይጎዱ ማድረግ ተችሏልም ብለዋል። በተያዘው የበጋ ወራትም የተፋሰስ ልማት ስራው በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች መከናወን የጀመረ ሲሆን ከ131 ሺህ ሔክታር መሬት ለመሸፈን 278 ተፋሰሶች ላይ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የሚከናወን መሆኑን ነው አቶ መልካሙ የገለጹት።
በትግራይ ክልል የተቀናጀ የዘላቂ መሬት አያያዝ መርሃ ግብር እየተከናወነ ነው
Feb 4, 2025 106
መቀሌ ፤ጥር 27/2017 (ኢዜአ)፡- በትግራይ ክልል የተቀናጀ የዘላቂ መሬት አያያዝ መርሃ ግብር እየተከናወነ መሆኑን በክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ አስታወቀ። የልማት ፕሮግራሙ ካለፈው ዓመት ሐምሌ ወር ጀምሮ በክልሉ በአስራ አንድ ወረዳዎች እየተከናወነ ይገኛል። በክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ የዘላቂ መሬት አያያዝ ፕሮግራም አስተባባሪ መሐሪ ገብረመድህን፤ በክልሉ የተቀናጀ የዘላቂ መሬት አያያዝ መርሃ ግብር በተጠናከረ መልኩ መቀጠሉን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት በተጀመረው መርሃ ግብር በተመረጡ 11 ወረዳዎች 93 ሺህ 787 ሄክታር መሬት የሚሸፍን የዘላቂ መሬት አያያዝ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። ለፕሮግራሙ ማስፈፀሚያም ከግብርና ሚኒስቴር ከ452 ሚልዮን ብር በላይ በጀት የተመደበለት መሆኑን አንስተው፤ በልማት ፕሮግራሙ ከ171 ሺህ 400 በላይ ሰዎች በቀጥታ ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ጠቅሰዋል። ከተመረጡት ወረዳዎች መካከል በስምንት ተፋሰሶች ላይ የዝናብ ውሃ የሚይዙ አነስተኛ ጉድጓዶች መቆፈራቸውን አስታውሰው፤ እርከንም እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በፕሮግራሙ የተካተቱ አካባቢዎች እንዳይራቆቱ በዘላቂነት የእንስሳት መኖ የማልማት፣ ንብ ማነብ፣ የእንስሳት እርባታና የማድለብ ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑንም አንስተዋል።
በህዝብ ተሳትፎ የለሙት ተፋሰሶች ምርታማ እንድንሆን እያገዙን ነው -የድሬዳዋ አርሶአደሮች
Feb 4, 2025 88
ድሬዳዋ፤ ጥር 27/2017(ኢዜአ)፦ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የተፋሰስ ልማት በመስኖ ስራ ተሰማርተው ኑሯቸውን እንዲለውጡ እያገዛቸው መሆኑን የድሬዳዋ ገጠር ቀበሌዎች አርሶ አደሮች ተናገሩ። በተፋሰሱ የለሙ ስፍራዎች ዘላቂ ጥቅም እንዲሰጡ አርሶ አደሮቹ በመከለልና በመንከባከብ ላይ መሆናቸውም ተገልፅዋል። በድሬዳዋ አስተዳደር ባለፉት ዓመታት በህዝብ ተሳትፎ በ38 የገጠር ቀበሌዎች በተራቆቱ ተፋሰሶች ላይ በተከናወኑ የአፈርና የውሃ ጥበቃ ስራዎች ከ50 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት እንዲያገግም አስችሏል። ዘንድሮም ይህንኑ ስራ የሚያጠናክር የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት በ5ሺህ 550 ሄክታር መሬት ላይ እየተካሄደ ይገኛል። በልማቱ ላይ እየተሳተፉ የሚገኙ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደተናገሩት፥ ቀደም ባሉት ዓመታት የተከናወኑ ልማቶች የአካባቢያቸው የተፈጥሮ ፀጋ እንዲያገግምና የእርሻ መሬት ምርታማነት እንዲጨምር አግዟቸዋል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል የኡላን ኡሉል ቀበሌ አርሶ አደር በድሪ ኡስማኢል እንዳሉት፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ልማቱ ምንጮች እንዲመለሱ በማድረጉ ውሃ ገብ የሆኑ ቀበሌዎች በአነስተኛ መስኖ በመሰማራት ተጨማሪ ገቢ እያገኙ ናቸው። እኔ በተፋሰሱ ልማት ባገኘሁት ተጨማሪ መሬት ከተከልኳቸው ፍራፍሬዎች ሽንኩርት፣ቃሪያና ቲማቲም በየዓመቱ ተጨማሪ ገቢ እያገኘሁ ነው ብለዋል። ሌላኛው የለገዶል ቀበሌ አርሶ አደር አብዱልሐሚድ መሐመድ የተፋሰስ ልማቱ ጠፍተው የነበሩ የተፈጥሮ ደኖች ማገገማቸውን ጠቅሰው፥ አካባቢው ለግብርና ስራና ለኑሮ ምቹ እየሆነ መምጣቱን ገልፀዋል። ልማቱ ቀደም ሲል የነበረውን በጋራ የመስራት ባህል እያሳደገ በመምጣቱ የእርሻ ስራን የበለጠ ፍሬያማ እያደረገው ይገኛል ብለዋል። የተፋሰስ ልማቱ በአረንጓዴ አሻራ እና በሌማት ትሩፋት የሚከናወኑ ፕሮጀክቶች ውጤታማ እንዲሆኑ ማገዙንና የገጠሩን ህብረተሰብ ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ማስቻሉን የገለፁት ደግሞ የቢሻን በሄ ቀበሌ አርሶ አደር ዑመር ቢላል ናቸው። አርሶ አደሩ አክለው እንደገለፁት፥ በቀበሌያቸው የተካሄደው የተፋሰስ ልማት ቀደም ሲል በጎርፍ ይጠረግ የነበረን የእርሻ መሬት ለመከላከል ወሳኝ ሚና ተጫውቷል። የለገቢራ ቀበሌ ወጣት አርሶ አደር ኢብሳ ሙሳ በበኩሉ ባለፉት ዓመታት በግንዛቤ ዕጥረት የተሰሩትን እርከኖች እያፈረሱ ድንጋይ መሸጥ አሁን እየቀረ ነው ብሏል። በተለይም ወጣቶች ተደራጅተው ያለሙትን አካባቢዎች ከሰውና ከእንሰሳት ንክኪ በመከላከል የእንሰሳት መኖ በማምረት ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን ገልጿል። ከለውጡ ወዲህ በአስተዳደሩ እየተከናወኑ የሚገኙ የተቀናጁ የተፋሰስ ልማቶች ህብረተሰቡ ከተረጂነት ወደ አምራችነት እያሸጋገሩ መሆናቸውን በመግለፅ። የድሬዳዋ አስተዳደር የግብርና ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ አማካሪ ወይዘሮ ሚስራ አብደላ እንዳሉት፤የተፋሰስ ልማቱ የገጠርና የከተማ ነዋሪዎች ስጋት የሆነውን የጎርፍ አደጋ እያስቀረለት ነው። በጎርፍ የሚጠረግን እርሻ በመከላከል የገጠሩ ነዋሪ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን እንዲያረጋግጥ እያገዘ መሆኑን በማከል።