አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
ነፋሻማው የጎዴ ፓርክ በወጣቶች ተመራጭ የመዝናኛ ሥፍራ ሆኗል
Feb 19, 2026 59
ጎዴ፤ የካቲት 12/2018 (ኢዜአ) ፡-ነፋሻማው የጎዴ ፓርክ በወጣቶች ተመራጭ የመዝናኛ ሥፍራ ሆኗል። በሶማሌ ክልል ጎዴ ከተማ የህዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ የመሰረተ ልማት፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ አገልግሎት ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተከናወነ ይገኛል። የከተማዋን ውበት የሚገልጡና የክልሉን እድገት የሚያፋጥኑ የወጣቶች መዝናኛና መናፈሻ ስፍራዎች መገንባታቸው ደግሞ የአካባቢውን ገጽታ ከመቀየር አኳያ ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው። በሞቃታማዋ ጎዴ ከተማ የተገነባው የክፍለ ዘመን መዝናኛ ፓርክ የዚሁ አካል ሲሆን በፓርኩ የሚገኙ እጽዋት አካባቢውን ነፋሻማ በማድረግ ለወጣቶች አማራጭና ተመራጭ መዝናኛ ሥፍራ ሆኗል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የከተማዋ ወጣቶች ፓርኩ ውብና አረንጓዴ በመሆኑ ሞቃታማውን የአካበቢውን አየር ጸባይ ነፋሻማና ምቹ አድርጎታል ይላሉ። የከተማዋ ወጣቶች ለመዝናናትም ሆነ ለንባብ የሚመርጡት ቦታ መሆኑንም ተናግረዋል። ወጣት ሀምዛ አብዱልዋሃብ እንደሚለው ፓርኩ ወጣቶች ጊዜያቸውን በአልባሌ ስፍራ እንዳያሳልፉ አማራጭ መዝናኛ ሆኗል። ወደ ፓርኩ በተደጋጋሚ በመምጣት አንደሚያነብና እንደሚዝናናም ገልጿል። ለተለያዩ ዝግጅቶች ፓርኩን ተመራጭ መዳረሻ እንደሚያደርግ የገለጸው ደግሞ ወጣት ሳዳም ሁሴን ነው። ፓርኩ ከአካባቢው ወጣቶች ባለፈ ወደ ጎዴ ለሚመጡ እንግዶች ተመራጭ የመዝናኛ ቦታ መሆኑን ተናግሯል። ወጣት ዴቃ መሀመድ በበኩሏ የፓርኩ መገንባት ውብና አረንጓዴ አካባቢ በመፍጠር በነፋሻማ አየር ጊዜዋን አንድታሳልፍ ዕድል መፍጠሩን ገልጻለች። የጎዴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አብዱላሂ አሊ፣ ከተማዋን አረንጓዴና ዉብ የማድረግ ሥራዎች በስፋት እየተከናወኑ ነው ብለዋል። ፓርኩ ለወጣቶች አማራጭ የመዝናኛ ቦታ ከመሆን ባለፈ ለአካባቢው ነዋሪዎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል።
አዲስ አበባ በንፅህና አጠባበቅ ረገድ እያከናወነች ያለው ሥራ በአርዓያነት ይጠቀሳል
Feb 19, 2026 63
አዲስ አበባ፤ የካቲት 12/2018 (ኢዜአ)፡- አዲስ አበባ በውኃና በንፅህና አጠባበቅ ላይ እያከናወነች ያለው ሥራ በአርዓያነት የሚጠቀስ መሆኑን በኢትዮጵያ የሕንድ አምባሳደር አኒል ኩማር ገለጹ። በአጠቃላይ ኢትዮጵያ በመሠረተ ልማት ግንባታ እያከናወነች ያለውን ተግባርም አድንቀዋል አምባሳደሩ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ። በተጨማሪም ኢኮኖሚዋን ለማሳደግ እየወሰደቻቸው ያሉ እርምጃዎች ለእድገቷ ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ገልጸዋል። በሌላ በኩል በተለያዩ ከተሞች የሚከናወኑት የኮሪደር ልማት ሥራዎች ትምህርት የሚወሰድባቸው መሆናቸውን ነው ያስረዱት። እንዲሁም አዲስ አበባ ከውኃና ንፅህና አጠባበቅ ጋር በተያያዘ እያከናወነቻቸው ያሉ ሥራዎች ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም እንደ ትልቅ ማሳያ የሚሆኑ ናቸው ብለዋል። ለአብነትም በርካታ የሕዝባዊ መገልገያ ስፍራዎች እና የፍሳሽ ቆሻሻ ማጣሪያ ጣቢያ መገንባትን ጨምሮ በደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ላይ እየተሠራ ያለውን ሥራ አድንቀዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Feb 16, 2026 146
ነገሌ ቦረና፤ የካቲት 9/2018(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ቦረና ዞን በመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ ነው። ምስራቅ ቦረና በአብዛኛው የእንስሳት እርባታ የሚካሄድበት ቆላማ፣ ዝናብ አጠር እና ደረቃማ ዞን እንደሆነ ይታወቃል። የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ፣ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን መትከል፣ የውሃ አማራጮችን ለይቶ መጠቀምና ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን መስኖን ማስፋት የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ መንግስት እያከናወናቸው ካሉ ተግባራት መካከል ይጠቀሳል። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ኩልሌ ሸና ፤በዞኑ ከለውጡ ዓመታት ወዲህ ተግባራዊ የተደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በሰው ሰራሽ እና በተፈጥሮ አዳጋዎች ሳቢያ የተራቆቱ አካባቢዎችን መልሶ ለማልማት እያስቻለ ነው ብለዋል። በዘንድሮው ዓመትም በ6 ሺህ ሔክታር መሬት ላይ ሁለንተናዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ለመጪው ክረምት በዞኑ በሚገኙ ዘጠኝ ወረዳዎች የደን፣ የጥላ ዛፍ ፣ የእንስሳት መኖና የፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞችን ለመጠበቅና ለመንከባከብ ሰፊ ስራ ተሰርቷል ያሉት ምክትል ኃላፊው በዚህም አብዛኛው ችግኝ መጽደቁን ጠቅሰዋል፡፡ በተለይም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተተከሉ የጽድ፣ ግራቪሊያ፣ ማንጎ፣ ፓፓያ፣ የእንስሳት መኖ እና የደንና የጥላ ዛፎች በተሻለ ሁኔታ መጽደቃቸውንም ለአብነት አንስተዋል። በዞኑ ሊበን ወረዳ የጎቢቻ ነዋሪ ሀጂ ቀራርሳ ጉራቻ፤ ባለፉት አመታት በደኖች ላይ በደረሰ ጉዳት ድርቅና የአካባቢ መራቆት ሲያስከትል መቆየቱን ያስታውሳሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተለያዩ ችግኞችን በመትከል የተፈጥሮ ሀብቱን መልሶ ለመተካት እየተደረገ ካለው ጥረት ባሻገር ችግኞቹን መትከልና መንከባከብ ለተሻለ ውጤት እንደሚያበቃ ነው የጠቀሱት። አቶ አብዲ ሮባ የዚሁ ወረዳና ቀበሌ ነዋሪ ሲሆኑ በየአመቱ በአካባቢው በሚከሰተው ድርቅ የወንዞችና ምንጮች መድረቅ፤ የእንስሳት መኖና የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ላይ ችግር እንደሚያጋጥም ገልጸዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ተግባራዊ በተደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ማህበረሰቡ የተሻለ ግንዛቤ ለመያዝ መቻሉንና ለውጥ መመዝገቡን ነው የገለጹት። በዚህም ማሕበረሰቡ ችግኞችን ከመትከል ባለፈ እንክብካቤም እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በተያዘው ዓመትም በተመሳሳይ መልኩ በመርሃ ግብሩ በመሳተፍ ዘላቂ ልማትና የምግብ ዋስትናን በሚያረጋግጡ ስራዎች ላይ የማተኮር እቅድ እንዳላቸው ጠቁመዋል፡፡ በምስራቅ ቦረና ዞን በ9 ወረዳዎች ባለፈው አመት በአረንጓዴ አሻራ ከተተከለው ችግኝ ውስጥ ከ75 በመቶ በላይ መጽደቁን መረጃዎች ያመለክታሉ።
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያስመዘገበችውን ስኬት አዲስ አበባ በራሷ ትናገራለች
Feb 15, 2026 135
አዲስ አበባ፤ የካቲት 8/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያስመዘገበችውን ስኬት አዲስ አበባ በራሷ ትናገራለች ሲሉ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ፡፡ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሃሙድ አሊ ዩሱፍ የ39ኛው የመሪዎች ጉባኤ መጠናቀቅን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ የኮሚሽኑ ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም በአረንጓዴ አሻራ ለተመዘገበው ስኬት እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ያሳዩት ቁርጠኝነት በተግባር የሚታይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአረንጓዴ አሻራ የተመዘገበውን ውጤት የአዲስ አበባ ከተማ በራሷ ትናገራለች ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ በማዘጋጀት የአፍሪካ አቋም ለማሳወቅ ማጣቀሻ የሚሆን ሰነድ መጽደቁን ተናግረዋል፡፡ ጉባኤው በአየር ንብረት ፋይናንስ፣ ተጽዕኖን በመቋቋምና በሀይል ሽግግር የአፍሪካን ድምጽ የሚያንጸባርቅ አቋም የተያዘበት መሆኑን አንስተዋል፡፡ አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ የበካይ ጋዝ ልቀት ተጽዕኖ ከ4 በመቶ እንደማይበልጥ በማንሳት፤ በብክለት የምትጎዳው ግን የላቀ ነው ብለዋል፡፡ በመሆኑም የአፍሪካ ሕብረት አባል ሀገራትን የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን መቋቋም የሚያስችል የማገገሚያ ዕቅድ እንዲያወጡ መደገፍ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡
የተፋሰስ ልማት ሥራው አርብቶ አደሩ ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን በእርሻ ዘርፍ እንዲሰማራ ያግዛል
Feb 15, 2026 159
ሠመራ፤ የካቲት 8/2018 (ኢዜአ)፡- በአፋር ክልል የሚከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ አርብቶ አደሩ ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን በእርሻ ዘርፍም እንዲሰማራ ያግዛል ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መሥተዳድር አወል አርባ ተናገሩ። የአፋር ክልል የ2018ዓ.ም የተፋሰስ ልማት ማስጀመሪያ መርሐ-ግብር "የተቀናጀ ማኅበረሰብ አቀፍ የተፋሰስ ልማት ለምግብ ሉዓላዊነነት ስኬት" በሚል መሪ ሐሳብ በአውሲ ረሱ ዞን አደአር ወረዳ ተጀምሯል። ርዕሰ መሥተዳድር አወል በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የተፋሰስ ልማት ሥራዎችን ማጠናከር አርብቶ አደሩ ሕብረተሰባችን ከሚታወቅበት የኑሮ መሠረት ጎን ለጎን በእርሻ ሥራ እንዲሰማራ ጉልህ ድርሻ ይኖረዋል። የተፋሰስ ልማቱ በድርቅና ሌሎች አደጋዎች ምክንያት እየተመናመነ የመጣውን የተፈጥሮ ሀብት በመመለስ ሕብረተሰቡ የምግብ ሉዓላዊነቱን እንዲያረጋግጥና ከተረጂነት እንዲወጣ ያስችላል ብለዋል። በተለይም የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙና ምርታማ እንዲሆኑ በማድረግ አርብቶ አደሩ ከእንስሳት እርባታ ጎን ለጎን የእርሻ ሥራውን በማሳደግ፤ ለእንስሳቱ መኖ፣ ለራሱም የምግብ ፍጆታውን እንዲሸፍን የሚያስችለው መሆኑን ተናግረዋል። በዘንድሮው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ከ200 ሺህ በላይ ሰዎችን በማሳተፍ ከ52 ሺህ ሔክታር በላይ የተፋሰስ ልማት ሥራ እንደሚከናወን ተገልጿል።
የበልግ እርሻን ቀድመው የሚጀምሩ አካባቢዎች በሚቀጥሉት አስር ቀናት የሚኖረውን የርጥበት ሁኔታ በአግባቡ ሊጠቀሙበት ይገባል
Feb 13, 2026 128
አዲስ አበባ፤ የካቲት 6/2018(ኢዜአ)፦ የበልግ እርሻን ቀድመው የሚጀምሩ የሀገሪቱ አካባቢዎች በሚቀጥሉት አሥር ቀናት የሚኖረውን የርጥበት ሁኔታ በአግባቡ እንዲጠቀሙበት ኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ከየካቲት 4 እስከ የካቲት 13 ቀን 2018 ዓ.ም ባሉት አሥር ቀናት የሚኖረውን የአየር ሁኔታ ትንበያ ይፋ አደርጓል፡፡ ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፣ የበልግ እርሻ እንቅስቃሴ ቀድመው የሚጀምሩ አካባቢዎች የሚገኘውን እርጥበት በአግባቡ እንዲጠቀሙበት አሳስቧል። በሚቀጥሉት አሥር ቀናት በደቡብ ምዕራብ፣ በስምጥ ሸለቆና አዋሳኝ አካባቢዎች ላይ አነስተኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖር ገልጿል፡፡ በተጨማሪም በመካከለኛውና በደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች ላይ የደመና ሽፋን እንደሚጨምር አመልክቷል፡፡ በጋምቤላ፣ በሰሜን ምዕራብ፣ በሰሜን ምስራቅና በደቡብ ምስራቅ አካባቢዎች የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን ከ32 ዲግሪ ሴልሺየስ በላይ ሆኖ እንደሚቀጥል ተቋሙ ጠቁሟል። በቀጣይ የሚኖረው የአየር ሁኔታ ለቋሚ ተክሎች የተሻለ እድገት እንዲያገኙ ያግዛል፣ ለአርብቶ አደሩ የግጦሽ ሳርና የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ለማሻሻል ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር እንዲሁም ለበልግ እርሻ ማሳን ቀድሞ ለማዘጋጀትና የአፈር ውስጥ እርጥበትን ለማሻሻል እንደሚረዳም ጠቅሷል፡፡ ሆኖም የእርጥበት መጠን ለሰብል ዝርያ የሚበቃ ባለመሆኑና ደረቅ አየር ሁኔታም ስለሚስተዋል አርሶ አደሩ ይህንን ተገንዝቦ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል። በሚቀጥሉት አሥር ቀናት በአብዛኞቹ ተፋሰሶች ላይ ደረቃማ የአየር ሁኔታ የሚጠበቅ በመሆኑ የገጸ-ምድር ውሃ ፍሰት ሊቀንስ እንደሚችል ተገልጿል። በተለይም በባሮ አኮቦ፣ በኦሞ ጊቤ፣ በስምጥ ሸለቆና በገናሌ ዳዋ ተፋሰሶች ላይ ዝቅተኛ የውሃ ፍሰት እንደሚኖር የተገለጸ ሲሆን በውሃ አጠር አካባቢዎች የሚገኙ ነዋሪዎች ውሃን ከብክነትና ከብክለት እንዲከላከሉ፣ እንዲሁም አማራጭ የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት መንገዶችን እንዲጠቀሙ ጥሪ ቀርቧል። በሚቀጥሉት አሥር ቀናት ለበልግ እርሻ ዝግጅትና ለቋሚ ተክሎች እንክብካቤ አመቺ ቢሆኑም ለዝርያ የሚበቃ ዝናብ ባለመኖሩና የውሃ መጠን ሊቀንስ ስለሚችል አስፈላጊው ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ ተመላክቷል።
ኢትዮጵያ በውኃ ዘላቂነትና ተደራሽነት ረገድ ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተች ነው
Feb 12, 2026 161
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ በውኃ ዘላቂነትና ተደራሽነት ረገድ ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተች መሆኗን የአፍሪካ ኅብረት የኢኮኖሚ፣ ማኅበራዊና ባህላዊ ምክር ቤት ሴክሬታሪያት ገለጸ። የአፍሪካ ኅብረት የኢኮኖሚ፣ ማኅበራዊና ባህላዊ ምክር ቤት ሴክሬተሪያት ኃላፊ ዊሊያም ካሪው፤ የኢትዮጵያ መንግሥት እያሳየ ያለው የአመራር ሚና ለአፍሪካ ኅብረት እጅግ መሰረታዊ መሆኑን ጠቁመዋል። የኅብረቱ አባል ሀገራት በማንኛውም አባላት ዘንድ የተዘረጉ መልካም ተሞክሮዎችንና ፖሊሲዎችን በአርዓያነት መጠቀም እንዳለባቸውም ለኢዜአ ተናግረዋል። በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ መንግሥት ለዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ተደራሽነት አስተዋጽኦ የሚያደርጉ ፖሊሲዎችንና አሠራሮችን መዘርጋቱን ገልጸው፤ ይህም ለሌሎች የአፍሪካ ኅብረት አባል ሀገራት መልካም ተሞክሮ መሆኑን አስታውቀዋል። በተወሰዱ የፖሊሲ ለውጦችና ቆራጥ የአመራር ሰጭነት ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን በመትከል ያስመዘገበችውን ስኬትም አድንቀዋል። ይህ ትልቅ ቁጥር መሆኑን ጠቁመው፤ የአመራርና ትክክለኛ ፖሊሲዎች ውጤት መሆኑን አስረድተዋል።
የተፋስስ ልማት ሥራ የአፈር ለምነትን በመጠበቅ ምርታማነትን በማሳደጉ አጠናክረን ቀጥለናል
Feb 12, 2026 125
ወልቂጤ፤ የካቲት 5/2018 (ኢዜአ)፡-የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈር ለምነትን በመጠበቅ ምርታማነትን እያሳደገ በመሆኑ ዘንድሮም አጠናክረው መቀጠላቸውን የጉራጌ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የአፈር ለምነትን በመጠበቅና የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ በማድረግ ምርታማነትን እያሳደገ በመሆኑ ዘንድሮም ልማቱን ማጠናከራቸውን ገልጸዋል። በጉራጌ ዞን የእኖር ኤነር መገር ወረዳ አርሶአደር በደዊ ታቅንዳ በተፋሰስ ልማት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ መጀመሩ በጎርፍ ተጠርጎ ይወሰድ የነበረ ለም አፈር ጥቅም ላይ ለማዋል አስችሏል ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ ሥራዎች የተራቆቱ መሬቶች ማገገማቸው እና የደረቁ ምንጮች ዳግም መፍለቃቸው የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ጉልህ ሚና ማበርከታቸውን ተናግረዋል። በዚህም በዘንድሮ የበጋ ወራት የተፋሰስ ልማት ሥራ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን ጠረጴዛማ የእርከን ልማት ሥራዎችን እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሌላኛው የእዣ ወረዳ አርሶ አደር ወይዘሮ ሙርጋት ታቅንዳ በበኩላቸው ባለፉት ተከታታይ ዓመታት የተከናወነው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ መሬታቸውን ከመሸርሸር መታደጉን ገልጸዋል። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ የመሬት ለምነትን በመመለስ ምርታማነትን እያሳደገ በመሆኑ በዘመቻው በንቃት እየተሳተፉ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ የተጎዱ መሬቶች መልሰው እንዲያገግሙና ምርታማነታቸው እንዲጨምር ማድረጉን የተናገሩት ሌላኛው የእኖር ወረዳ አርሶ አደር መህዲ ደሊል ናቸው። የተፋሰስ ልማት ሥራው እየተመናመኑ የነበሩ የደንና የውኃ ሀብቶች እንዲመለሱ ማስቻሉንም ገልፀዋል ። የለሙ አካባቢዎችን ከሰውና ከእንስሳት ንኪኪ በመጠበቅ ለመኖ ልማትና ለንብ ማነብ ሥራ በማዋል ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እያስቻሉ መሆናቸውንም ጠቁመዋል። የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ በበኩላቸው እንዳሉት ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራዎች ውጤት ተመዝግበዋል። በተለይም ተዳፋታማ በሆኑ አካባቢዎች ጠረጴዛማ እርከን በመስራት ከምርት ውጭ የነበሩ መሬቶች አገግመው በተለያዩ ሰብሎች እንዲለማ ከመደረጉ ባለፈ ለንብ ማነብ ሥራ እየዋሉ መሆኑን ገልጸዋል። የደረቁ ምንጮችና በጎርፍ በመሸርሸር የተጎዱ መሬቶች ማገገማቸው የግብርና ምርትና ምርታማነትን እያሳደገው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የተመዘገቡ ተጨባጭ ውጤቶች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ በማድረጋቸው በዘንድሮ ተፋሰስ ልማት የወጣቶችና የሴቶች ተሳትፎ በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩን ገልጸዋል። በዘንድሮ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ በዞኑ በ23 ሺህ ተፋሰሶች ላይ 88 ሺህ 581 ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች በአፍሪካ የውሃ ዋስትናን ለማረጋገጥ አርዓያነት ያለው ተግባር ነው
Feb 9, 2026 222
አዲስ አበባ፤ የካቲት 2/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራና ተፋሰስ ልማት ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች በአፍሪካ የውሃ ዋስትናን ለማረጋገጥ አርዓያነት ያለው ተግባር ነው ሲሉ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በአፍሪካ ሕብረት የኢኮኖሚ፣ ማህበራዊና ባህል ምክር ቤት "የአጀንዳ 2063 ግቦች ለማሳካት ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ" የሚለውን የ39ኛው የሕብረቱን መሪ ቃል በተመለከተ የሲቪል ማህበረሰብ ቅድመ ስብሰባ አካሂዷል፡፡ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በአፍሪካ ከ400 ሚሊየን በላይ ዜጎች የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ችግር ይገጥማቸዋል፡፡ በአህጉሪቱ ከ700 ሚሊየን በላይ ዜጎች በተለይም ወጣቶች፣ ሴቶችና የገጠር ነዋሪዎች የንጽህና አጠባበቅ (ሳኒቴሽንና ሀይጅን) ጉድለት ችግር እንደሚያጋጥማቸው ገልጸዋል፡፡ የአፍሪካ ሕብረትም የአጀንዳ 2063 አንዱ ግብና የዘንድሮው ዓመት መሪ ሀሳብ ያደረገውም ውሃ የዜጎች መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን በመገንዘብ ነው ብለዋል፡፡ በአህጉሪቷ ዘላቂ የውሃ አቅርቦት እና የአካባቢ ንጽህናን ማረጋገጥ ዘላቂ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ለማስመዝገብ እና ውሃ ወለድ በሽታን ለመከላከል ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል፡፡ የውሃ ሀብታችን የኢኮኖሚያችን አቅም፣ የህልውናችን መሰረት ነው ያሉት ሚኒስትሩ፤ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታተ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ትብብር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ ባለፉት ሰባት ዓመታት ዘላቂ የውሃ ሀብት ልማትን ለማረጋገጥ ተጨባጭ የተግባር ውጤት ማስመዝገቧን ገልጸው፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን ተክላለች ብለዋል፡፡ እነዚህ የተተከሉ ችግኞች የፅድቀት መጠንም ከ90 በመቶ በላይ ሲሆን፤ በዚህ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ከፍተኛ መጠን ያለው ውሃ ማዳን እንደተቻለ ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ እና ተፋሰስ ልማት ያስመዘገበቻቸው ስኬቶች አፍሪካውያን በትብብር የንጹህ መጠጥ ውሃና ንጽህናን ማረጋገጥ እንደሚችሉ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የወንዝ ዳርቻ እና ኮሪደር ልማት ስራ በአዲስ አበባ ከተማ ጀምራ ወደ ተለያዩ ክልሎች ማስፋቷን ያነሱት ሚኒስትሩ፤ ይህም የወንዞችን ውበትና የውሃ ንጽህናን መጠበቅ አስችሏል ብለዋል፡፡ የአፍሪካ የገጸ ምድርና ከርሰ ምድር የውሃ ሀብት እንዳይበከል አስፈላጊውን የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ማከናወን እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡ በመሆኑም እንደ አፍሪካ በጋራ በመተባበር ከቻልን አንዳችን ለአንዳችን በረከት እንሆናለን፤ ንጹህ የከርሰ ምድር ውሃ ይኖረናልም ብለዋል፡፡
የበልግ አብቃይ የሆኑት የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ ይኖራቸዋል
Feb 9, 2026 182
አዳማ ፤ የካቲት 2/2018 (ኢዜአ)፦በአብዛኛው የበልግ አብቃይ የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛ እና ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚያገኙ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የበጋ ወቅት የአየር ፀባይ ትንበያ ግምገማና የበልግ ወቅት ትንበያ ይፋ ማድረጊያ መድረክ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በአዳማ ማካሄድ ጀምሯል። ኢንስቲትዩቱ በዚሁ መድረክ ላይ ይፋ እንዳደረገው የበልግ ወቅት የአየር ትንበያ በልግ ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚኖራቸው ጠቁሟል። በዚሁ መሰረት የቦረና እና ጉጂ ዞኖች ፣ሲዳማ እና ደቡብ ኢትዮጵያ ከመደበኛ በላይ ዝናብ ያገኛሉ። እንዳሁም የሶማሌ ክልል ደቡባዊ ክፍል እና የምእራብና ደቡብ ምእራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች ደግሞ መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚያገኙ ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል። በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት እየተስተዋሉ ከሚገኙ የአየር ሁኔታ ክስተቶች ላይ በመነሳት በሰሜን ምእራብ በመካከለኛው፣ በምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይም መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ ይኖራል። በሌላ በኩል የቀኑ ከፍተኛ ሙቀት መጠን በሰሜን ምስራቅ፣ በሰሜን ምእራብ እና በደቡብ ምእራብ አካባቢዎች ላይ ከመደበኛ በላይ እንደሚሆን የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ። የበልግ ወቅት የዝናብ አጀማመር በደቡብ አጋማሽ አካባቢዎች ላይ ቀደም ብሎ የሚጀመር ሲሆን በአወጣጥ ረገድ ግን በተወሰኑ ቀናቶች ዘግይቶ ይወጣል ተብሏል። ይህን የዝናብ መጠንና ስርጭት በአግባቡ መጠቀምና በዚህ ወቅት የሚካሄደውን የግብርና እንቅስቃሴ እና ሌሎች ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ስራዎች ከባለሙያዎች ጋር በመመካከር ማከናወን ያስፈልጋል ተብሏል። በዘንድሮ የበልግ ወራት የዝናብ መጠንም ለግብርና ስራ አመቺ መሆኑ ተገልጿል።
ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁሉን አቀፍ የልማት ጉዞ ለማሳካት የአየር ንብረት መረጃዎችን በአግባቡ ስራ ላይ ማዋል ይገባል
Feb 9, 2026 173
አዳማ ፤ የካቲት 2/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁሉን አቀፍ የልማት ጉዞ ለማሳካት የአየር ንብረት መረጃዎችን በአግባቡ ስራ ላይ ማዋል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስገነዘበ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የበጋ ወቅት የአየር ፀባይ ትንበያ ግምገማና የበልግ ወቅት ትንበያ ይፋ ማድረጊያ መድረክ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በአዳማ ማካሄድ ጀምሯል። መድረኩን በንግግር የከፈቱት የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር አማካሪ አቶ ሞቱማ መቃሳ እንዳሉት፤ ኢንስቲትዩቱ የሚቲዎሮሎጂ መረጃዎችን አስተማማኝነትና ቅልጥፍና በማሳደግ ሁለንተናዊ ልማትን ለማሳካት በሚደረገው ጥረት የበኩሉን እየተወጣ ነው። የሚቲዎሮሎጂ መረጃዎቹ ለግብርና፣ ለውሃና ኢነርጂ፣ ለትራንስፖርት፣ ለአካባቢ ጥበቃና ለአደጋ አመራር፣ ለኢንሹራንስና ለኢንዱስትሪ ዘርፎች በሳይንሳዊ መንገድ ተተንትነው መቅረባቸውን ገልፀዋል። እነዚህ የትንበያና ቅድመ ማስጠንቀቂያ መረጃዎች ለውሳኔ ሰጪዎችና ለተጠቃሚው ማህበረሰብ ከፍተኛ እገዛ አድርገዋል ብለዋል። ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁሉን አቀፍ የልማት ጉዞን ለማሳካት የአየር ንብረት መረጃዎችን በአግባቡ ስራ ላይ ማዋል እንደሚገባም አማካሪው አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ በበኩላቸው፤ ኢንስቲትዩቱ ከአየር ሁኔታና ፀባይ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን መረጃዎች በየወቅቱ ለተጠቃሚዎች እየሰጠ ይገኛል ብለዋል። የበጋ፣ የበልግ፣ የክረምት የአየር ሁኔታና ፀባይ ትንበያዎችና የቅድመ ማስጠንቀቂያ አገልግሎቶች ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በማዋል ውጤት ማስገኘታቸውን አንስተዋል። የበጋ ወቅት የአየር ሁኔታ በጊዜና በቦታ ትንበያ ከክስተቶች ጋር በእጅጉ የተጣጣመ መሆኑን አስረድተዋል። በዛሬው መድረክም የአገራችን የበልግ ወቅት ዝናብ አዎንታዊና አሉታዊ ተፅእኖን ለመቋቋም ግንዛቤ ለመፍጠር ያለመ ነው ብለዋል። ህብረተሰቡም በኢንስቲትዩቱ የሚሰጠውን ትንበያ እና ቅድመ ማስጠንቀቂያ መረጃ በሚገባ በመከታተል ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባው ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል፡
በጋምቤላ ክልል የሙቀቱ መጠን እየጨመረ በመምጣቱ በመንግስት የስራ ስዓት ላይ ለውጥ ተደረገ
Feb 7, 2026 184
ጋምቤላ፤ ጥር 30 /2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል የሙቀቱ መጠን እየጨመረ በመምጣቱ የመንግስት የስራ ስዓት ላይ ለውጥ መደረጉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድርና ካቢኔ ጉዳዮች ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የፅህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ኡቶው ኡኮት፤ የሙቀቱ መጠን እየጨመረ በመምጣቱና ለስራ አስቸጋሪ በመሆኑ ከፊታችን ሰኞ የካቲት 2 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የስራ ሰዓት ለውጥ መደረጉን ገልጸዋል። የተደረገው የሰዓት ለውጥ ለቀጣዮቹ ሶስት ወራት የሚቀጥል መሆኑን ጠቁመው በዚሁ መሰረት ሁሉም የመንግስት ተቋማት ተግባራዊ እንዲያደርጉ አሳስበዋል። በለውጡ መሰረትም ቀደም ሲል ከጧቱ 1:00 እስከ 6: 30 የነበረው ከ1:00 አስከ 5:30 እንዲሆን እንዲሁም ከስዓት በኋላ ከ9:00 እስከ 11:30 የነበረው 10:00 እስከ 12:30 ይሆናል ብለዋል። የስራ ስዓት ለውጡ ወይና ደጋ የአየር ንብር ያላቸውን የመንጌሽና የጎደሬ ወረዳዎችን እንደማይጨምር የገለጹት ኃላፊው የክልሉ የመንግስት ሰራተኛች በተጠቀሰው ጊዜ ወደ ቢሮ በመግባት ስራቸውን በትጋት እንዲያከናውኑ አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ሜትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የጋምቤላ ክልል የሜትሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል ተወካይ ነብዩ ፈረደ፤ በአሁኑ ወቅት የክልሉ አማካይ የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን 41.4 ድግሪ ሴልሸስ መሆኑን ጠቁመዋል። የሌሊቱ ዝቅተኛው የሙቀት መጠን ደግሞ 25 ነጥብ 6 ድግሪ ሴልሸስ መሆኑን ጠቁመው ባለፉት ወራት የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን በአማካኝ ከ35 ድግሪ ሴልሸስ የለሊቱ ደግሞ 22 ዲግሪ ሸልሰስ በታች እንደነበር አስታውሰዋል። በክልሉ የሞቃታማ ወራት የሚባሉት የካቲት፣ መጋቢትና ሚያዚያ ወራት ሲሆኑ በእነዚህ ወራት ውስጥ የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን እስከ 45 ድግሪ ሴልሸስ የሚደርስበት ጊዜ እንዳለ መረጃዎች ይጠቁማሉ።
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የበጋ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው
Feb 7, 2026 144
ጭሮ፤ ጥር 30/2018 (ኢዜአ) ፡-በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ከ700 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የበጋ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። በዞኑ እየተከናወነ ያለውን የበጋ የአካባቢ ጥበቃ ስራ በተመለከተ ኢዜአ የሚመለከታቸውን የስራ ሃላፊዎችና የልማቱ ተሳታፊ አርሶ አደሮችን አነጋግሯል። በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሐረርጌ ዞን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ሃላፊ ሸረፍ አብደላ፤ በዞኑ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ በተለይም ተራቁተው የቆዩ ተራራማ አካባቢዎች እንዲያገግሙ ማድረጉን ገልጸዋል። በልማቱ የተገኘውን ውጤት ተከትሎ በበጋና ክረምት ጭምር የልማት ስራው ተጠናክሮ የቀጠለ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም መሰረት በዘንድሮው የበጋ ወራት ከ700 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ በ455 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በልማቱ እስካሁን ከ109 ሺህ 700 ኪሎ ሜትር በላይ የአፈርና የድንጋይ እርከን ስራ በማከናወን የእቅዱን 95 በመቶ ማሳካት የተቻለ መሆኑን ተናግረዋል። ከልማቱ ተሳታፊ አርሶ አደሮች መካከል አርሶ አደር ጀማል አብዶ፣ ወይዘሮ ነስራ አብዱሬ እና አብነት ጉልላት፤ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራው አካባቢን ከመጠበቅም ባለፈ ለምርታማነት መጨመር ትርጉም ያለው በመሆኑ እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርታማነትን ከማሳደግም ባለፈ የጎርፍ አደጋን ለመከላከል ሁነኛ መፍትሄ መሆኑን ተናግረው አጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን ገልጸዋል።
የተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርትና ምርታማነታችንን አሳድጎልናል- አርሶ አደሮች
Feb 6, 2026 126
ወላይታ ሶዶ ፤ ጥር 29/2018 (ኢዜአ)፡- የተፋሰስ ልማት ስራው የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርትና ምርታማነታቸውን ማሳደጉን በደቡብ ኢትዮጵያ እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች የሚገኙ አርሶ አደሮች ተናገሩ። በደቡብ ኢትዮጵያ እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች ነዋሪ የሆኑ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ እየተካሔደ ያለው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የመሬት ለምነትን በመመለስ ምርታማነት ለማሳደግ እያስቻለ ነው። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በወላይታ ዞን ኦፋ ወረዳ ነዋሪ አቶ ተስፋዬ ሜጊሶ እና ማርታ አዋሾ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መጀመሩ በጎርፍ እየተጠረገ ይወሰድ የነበረውን ለም አፈር ጥቅም ለይ ለማዋል አስችሎናል ይላሉ። በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው ሳቢያ የደረቁ ምንጮች ዳግም እንዲፈልቁ በማድረጉ የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲለሙ ማድረጉን አመልክተዋል። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሀዲያ ዞን ምስራቅ ባድዋቾ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አበራሽ አቡቶ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሰራው የተራቆጡ አካባቢዎች ዳግም እንዲለሙ ማድረጉን ተናግረዋል ። በዚህም የተለያዩ የጓሮ አትክልት በማምረት ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን ጠቅሰው የተፋሰስ ልማት ስራን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ነው ያመለከቱት ። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ ፋኖሴ መኮንን በበኩላቸው፤ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራው ምርታማነት በማሻሻል ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ ነው። ባለፉት ዓመታት በተሰራው ስራ እንደ ሀገር አደጋ ላይ ከነበሩ 54 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ውስጥ 33 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ የሚሆነው ዳግም እንዲያገግም ለማድረግ ተችሏል ነው ያሉት።። በተለይም የአፈር ለምነትን በመጨመር፣ የደረቁ ምንጮች ዳግም እንዲፈልቁ በማድረግ እና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ጉልህ ሚና መጫወቱንም ነው ያነሱት። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራው እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተደረገ ያለውን ጥረት ለማሳካት የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዘንድሮው ዓመትም 25 ሚሊዮን የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በ23 ሺህ ተፋሰሶች ላይ 4 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው የተፋሰስ ልማት ስራ ላይ እየታየ ያለው የህብረተሰብ የተሳትፎ ባህል መጠናከር እንደሚገባውም አሳስበዋል።
የሐረማያ ሐይቅ የቱሪስት መዳረሻነት የማበልጸግ ስራ በተቀናጀ መንገድ በመከናወን ላይ ይገኛል
Feb 2, 2026 202
ሐረማያ ፤ጥር 25/2018 (ኢዜአ) ፡-የሐረማያ ሐይቅን የቱሪስት መዳረሻነቱን የማበልጸግ ስራ በተቀናጀ መልኩ እየተካሔደ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ገለጸ። በማያ ከተማ አስተዳደር ከሚገኙት የቱሪስት መዳረሻዎች መካከል የሐረማያ ሃይቅ እንዱ ነው። ለበርካታ ዓመታት ደርቆ የነበረው ሐይቁ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና የአረንጓዴ አሻራ ስራዎች ትኩረት ተደርጎ በመከናወናቸው ወደ ቀድሞው ይዞታው መመለስ ችሏል። የከተማ አስተዳደሩ እና የአካባቢው ማህበረሰብ ሃይቁን እያለማውና እየተንከባከበው በመሆኑም የጎብኚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን የኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ጀሚላ ሲምቢሩ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ሐይቁ ከመዝናኛነቱ ባለፈ ለወጣቶች የስራ እድል እየፈጠረ የሚገኝ ሲሆን በዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የማጎልበት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። አካባቢው ትልልቅ እሴቶችና ጸጋዎች የሚገኙበትና በኪነ ጥበቡም ዘርፍ ስመ-ጥር አርቲስቶች የፈለቁበት መሆኑንም ይገልፃሉ። የአካባቢውን ባህል፣ ኪነ ጥበቡብና ቱሪዝሙ ዘርፉን እንደ አንድ ጸጋ በመጠቀምና ከቱሪዝም ጋር በማሰናሰል የዘርፉን ኢኮኖሚ ማሳደግና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። የማያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢፍራህ ወዚር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአፈርና ውሃ ጥበቃ እና በአረጓዴ አሻራ ስራ የተመለሰውን የሐረማያ ሃይቅ አጠቃቀምን የማስተካከል፣ የመጠበቅና የመንከባከብ ስራ እየተከናወነ ይገኛል። ሐይቁ ወደ ቀድሞ ቦታው መመለሱ ለጎብኚዎች እርካታን ከማጎናጸፉ ባለፈ ለአካባቢው ነዋሪዎችና ለወጣቶች የገቢ ምንጭ እየሆነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የሐረማያ ሐይቅ በተደረገለት እንክብካቤ ውብና ማራኪ የቱሪስት ቀልብ የሚስብ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፤ ለወጣቶችም የገቢ ምንጭ ማግኛ ሆኗል ያለው ደግሞ በኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የቱሪዝም ባለሙያ ኦሊያድ በሪሶ ናቸው። በአካባቢው ባለሀብቶችን በመጋበዝ ሎጆችና ሪዞርቶች በማስፋፋት የተሻሉ ስራዎችን መስራት እንደሚቻልም ነው አቶ ኦሊያድ አስተያየታቸውን የሰጡት። በሐረማያ ሐይቅ ላይ የጀልባ አገልግሎት የሚሰጠው ወጣት ሙርቲ አህመድ፤ጎብኚዎችን በጀልባ ከማስጎብኘት ስራ በተጨማሪ በአሳ ልማት ስራም መሰማራቱን ይገልፃል።
በአማራ ክልል የበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች ምርታማነት እንዲጎለብት አግዘዋል
Feb 2, 2026 228
ባህር ዳር፤ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፡- አማራ ክልል የበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርታማነት እንዲጎለብት እገዛ ማድረጋቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት፤ ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንዳሉት በክልሉ የበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርታማነት እንዲያድግ አግዘዋል። ስራውን በማስቀጠልም በያዝነው የበጋ ወራት በተለዩ ዘጠኝ ሺህ 206 ተፋሰሶች በ456 ሺህ 411 ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ለማከናወን ግብ ተይዞ ወደ ተግባር ተገብቷል። እስካሁን በተደረገ ጥረትም የዕቅዱን 37 በመቶ ማከናወን እንደተቻለ ጠቅሰው፤ በዚህም ከ3 ነጥብ 8 ሚሊዮን በላይ አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን ገልፀዋል። ከዚሁ በተጓዳኝም ለመጪው ክረምት ወራት የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ የሚሆን ቦታ የመለየትና ለተከላ የሚውል ከ አንድ ነጥብ 7 ቢሊዮን በላይ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን አንስተዋል። በተቀናጀ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ ላይ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል በደቡብ ጎንደር ዞን የፋርጣ ወረዳ አርሶ አደር ዓለሙ መንጌ በበኩላቸው፤ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ከህልውና ጋር የተያያዘ መሆኑን በመረዳት ተግባሩን በማጠናከር በየዓመቱ በራሳቸው ተነሳሽነት እያከናወኑ መሆናችውን አንስተዋል። ዘንድሮም በቀበሌያቸው በተጀመረው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ላይ በንቃት በመሳተፍ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት በቀበሌያቸው ያከናወኑት የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ የመሬቱን ለምነት በመመለስ ለምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ እንዳበረከተላቸው የገለፁት ደግሞ ሌላኛው የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ካሳሁን መንግስት ናቸው። ቀደም ሲል የተሰራው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ግማሽ ሄክታር የእርሻ ማሳቸውን ለምነት በመመለሱ እስከ አምስት ኩንታል ተጨማሪ ምርት እንዲያገኙ ማስቻሉን ገልፀዋል። የልማት ስራው ተጠቃሚነታቸውን በተጨባጭ እያሳደገ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ በበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራ ላይ እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት የተከናወነ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራም የደን ሽፋንን ከማሳደግ ባሻገር በግብርና ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ለውጥ ማስመዝገብ እንዳስቻለም ተመላክቷል።
የአረንጓዴ አሻራ፣ የተፋሰስ ልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማቶች የውሃ አዘል መሬቶችን ከመጠበቅ አኳያ ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው
Feb 2, 2026 206
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ፣ የተፋሰስ ልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማቶች የውሃ አዘል መሬቶችን ከመጠበቅ አኳያ ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ፡፡ ባለስልጣኑ የዘንድሮውን የዓለም የውሃ አዘል መሬቶች ቀን "የውሃ አዘል መሬት እና ሀገር በቀል እውቀት፤ የባህል ቅርሳችንን እናክብር" በሚል መሪ ቃል እያከበረ ይገኛል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የተለያዩ የውሃ አዘል መሬቶች እና የብዝሃ ህይወት ባለቤት ናት። እነዚህ ተፈጥሯዊ ጸጋዎች ተጠብቀው ለትውልድ እንዲሸጋገሩም ሀገር በቀል እውቀት እና ባህላዊ የጥበቃ ስልቶች ከፍተኛ ሚና ሲጫወቱ መቆየታቸውን ገልጸዋል። የውሃ አዘል መሬቶች ከፍተኛ ጥቅም እያስገኙ መሆኑን ጠቁመው የተበከለ ውሃን በተፈጥሯዊ መንገድ ማጣራት፣ የጎርፍ አደጋን መከላከል እና የአፈር እርጥበትን መጠበቅ እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም እና የአካባቢን ሙቀት መቀነስን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ በእነዚህ ወሳኝ የተፈጥሮ ሃብቶች ላይ የሚደርሱ ተግዳሮቶችን ለመፍታት ዘመናዊውን ሳይንሳዊ እውቀት ከሀገር በቀል ጥበብ ጋር አቀናጅቶ መተግበር እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተተገበሩ ያሉ የአረንጓዴ አሻራ እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች ለውሃ አዘል መሬቶች ደህንነት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን አረጋግጠዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአካባቢ ጥበቃና ደን ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ግዛቴ ግጄ፤ በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ውሃ አዘል መሬቶችን የመለየትና ተገቢውን ጥበቃ የማድረግ ተግባር በትኩረት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የአማራ ክልል የአካባቢ ጥበቃና ደን ባለሥልጣን ምክትል ዳይሬክተር አቶ በልስቲ ፈጠነ በበኩላቸው፤ በክልሉ የሚገኙ የውሃ አዘል ስፍራዎችን በዘላቂነት ለማልማት ዘመናዊ ሳይንሳዊ ዕውቀቶችን ከባህላዊ ጥበቃ ዘዴዎች ጋር በማቀናጀት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ማህበረሰቡ ስለ እርጥብ መሬቶች ፋይዳ ያለውን ግንዛቤ እንዲያሳድግና ከሀብቱ በሥርዓት ተጠቃሚ እንዲሆን ሰፊ የትምህርትና የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የኦሮሚያ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ ብርሃኑ ኢዳቲ ጠቁመዋል።
በዞኑ አርብቶ አደሩን በማሳተፍ ከ33 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው
Jan 31, 2026 221
ጂንካ፤ ጥር 23/2018(ኢዜአ):- በደቡብ ኦሞ ዞን አርብቶ አደሩን በማሳተፍ ከ33 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የአፈርና ውሃ ጥበቃና የግጦሽ ሳር መከለል ስራ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ ምንላርገው አዲሱ፣ በዞኑ በተጀመረው የተፋሰስ ንቅናቄ ከ16 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት 50 ንዑስ ተፋሰሶች የማልማት ስራ እንዲሁም በአርብቶ አደርና በዝቅተኛ አካባቢዎች ደግሞ ከ17 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የግጦሽ ሳር መከለል ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ በዞኑ ከ33 ሺህ ሄክታር መሬት የተፋሰስና የግጦሽ ሳር መከለል ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፥ የተፋሰስ ልማቱ በተከናወነባቸው ስፍራዎች ከ11 ሚሊየን በላይ ሀገር በቀል ችግኞች ተከላ ይከናወናል ነው ያሉት። በዘንድሮው ዓመት የተፋሰስ ልማት በሳይንሳዊ ጥናት የተደገፈ ስነ-አካላዊና ስነ-ህይወታዊ ስራዎች እንደሚከናወኑም ጠቁመዋል። ልማቱ የተከናወነባቸው አካባቢዎችን ከሰውና ከእንሰሳት ንክኪ ነፃ በማድረግ የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ስራ እንደሚሰራም ገልጸዋል። በዞኑ ሐመር ወረዳ እየተከናወነ ባለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የተሳተፉት ወይዘሮ አልጎ በሌ፥ በአካባቢው የቡስካ ጥብቅ ደን እንደሚገኝ ተናግረዋል። ቀደም ሲል ደኑ በሰውና በእንስሳት ጉዳት ይደርስበት እንደነበር አስታውሰው አሁን ላይ ደኑን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ነፃ በማድረግ የመጠበቅ ስራ ላይ እየተሳተፉ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በአካባቢያችን የተፋሰስ ልማት ከተጀመረ ወዲህ አካባቢው ለእርሻ ተስማሚ መሆን ጀምሯል ያሉት አቶ አስ ኦቶሎ ለእንስሳት የሚሆን በቂ የግጦሽ ሳር የምናገኝበት ዕድልንም እየፈጠረ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠት ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች ነው
Jan 29, 2026 178
አርባምንጭ፤ ጥር 21/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ዓለምአቀፍ ተግዳሮት ለሆነው አየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠት ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች መሆኗን የፕላንና ልማት ሚኒስቴር አስገነዘበ። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአካባቢ አየር ንብረት ለውጥ ዘርፍና የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ እየተካሄደ ነው። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴዔታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እንዲሁም የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ላይ በትኩረት እየሠራች ነው ብለዋል። ዓለምአቀፍ ተግዳሮት ለሆነው የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠትም ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች መሆኗን አስገንዝበዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብርን ጨምሮ በሀገር በቀል ስልቶች ለአየር ንብረት ለውጥ እየተሰጠ ባለው ምላሽም ተጨባጭ ውጤት መምጣቱን አረጋግጠዋል። የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ እንዳሉት፤ ዜጎች ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ የመኖር መብታቸውን ለማረጋገጥ የጽዱና አረንጓዴ ልማት ሥራዎች ተሠርተዋል። የከተሞች ኮሪደር ልማትን ጨምሮ የጽዱ ኢትዮጵያ፣ የወንዝ ዳርቻና የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቮች ለውጤቱ መገኘት ጉልህ ድርሻ አንዳላቸው አመልክተዋል። ባለፉት ስድስት ወራት የአካባቢ ቁጥጥር ሥርዓትን ለማጠናከር የወጡ ሕጎችና መመሪያዎች ተፈጻሚነት ላይ ተከታታይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች መሠራታቸውንም አንስተዋል። በዚህም የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ፣ በአካባቢ ማኅበራዊ ተጽዕኖ ግምገማ እንዲሁም በብዝኃ ሕይወት ጥበቃ ላይ የተሻለ ውጤት መምጣቱን አንስተዋል።
በተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር ለምነት በመጨመሩ የአርሶአደሮች ምርታማነት አድጓል
Jan 28, 2026 255
ወላይታ ሶዶ ፤ ጥር 20/2018 (ኢዜአ)፡- በተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር ለምነት በመጨመሩ ምርታማነታቸው ማደጉን በወላይታ ዞን የኦፋ ወረዳ አርሶ አደሮች ተናገሩ። "እመርታ በተቀናጀ ተፋሰስ ለብልፅግናችን!" በሚል መሪ ሃሳብ የ2018 ዓ.ም ዞናዊ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት የማስጀመሪያ መርሃ ግብር በዞኑ ኦፋ ወረዳ ቡሻ ቀበሌ ጋዬ ንዑስ ተፋሰስ ላይ ተካሄዷል። በወቅቱም ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ አርሶ አደሮች እንዳሉት፤ በተፋሰስ ልማት ስራው የአፈር ለምነት በመጨመሩ ምርታማነታቸው አድጓል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል አርሶ አደር በቀለ ቶጋ፤ ለበርካታ ዓመታት በተፋሰስ ልማት ስራ ላይ ሲሳተፉ መቆየታቸውን ገልፀው በአካባቢው የልማት ስራው ከመከናወኑ በፊት በነበረው የአፈር በጎርፍ መሸርሸር ሳቢያ መሬቱ ተራቁቶ እንደነበር ገልጸዋል። ሆኖም ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአፈር ለምነት እንዲጨምርና ምንጮች እንዲፈልቁ በማድረጉ በስራው በዘላቂነት እንድንሳተፍ መነሳሳትን ፈጥሮልናል ብለዋል። የአየር መዛባትና የአካባቢ መራቆት ከሁሉም በላይ አካል ጉዳተኞች ላይ የሚያደርሰው አሉታዊ ተጽዕኖ የከፋ በመሆኑ አካል ጉዳተኝነት ሳይበግረኝ የሚጠበቅብኝን እየተወጣሁ እገኛለሁ ያሉት ደግሞ አርሶ አደር መሰለ መንገሻ ናቸው። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው ከዚህ ቀደም የተራቆቱ አካባቢዎች አገግመው ምርት እንዲሰጡ ከማድረጉም ባሻገር ለኑሮ ምቹ አካባቢን ፈጥሮልናል ብለዋል። የአፈር ለምነት በጨመረባቸው እና ምንጭ በፈለቀባቸው አካባቢዎች የተለያዩ የጓሮ አትክልቶችን በማምረት ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ተናግረዋል። የኦፋ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አዲሱ ወርቁ በበኩላቸው፤የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ለዘላቂ የግብርና ልማት ወሳኝ በመሆኑ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በወረዳው በዘንድሮ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ሥራ ከ31 ሺህ በላይ ህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በ20 ንዑስ ተፋሰሶች ከ2 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት መታቀዱን ገልጸዋል። በዞኑ ባህል ሆኖ የቀጠለው የተፋሰስ ልማት ስራ በስነ-አፈር እና በስነ-አካላዊ ስራዎች የተራቆቱ አካባቢዎች በማገገማቸው ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱን የተናገሩት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ ዘማች ሶርሳ (ዶ/ር) ናቸው። ይህንን ውጤት ለማስቀጠል በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው በዘንድሮ የተፋሰስ ልማት ስራ በዞን ደረጃ በ315 ተፋሰሶች ከ46 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ለመሸፈን ታቅዶ ስራ መጀመሩን ነው የገለጹት። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የወላይታ ዞን ብልጽግና ፖርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አማረ አቦታ (ዶ/ር)፤ በዞኑ የተፋሰስ ልማት ስራ ከተጀመረ ወዲህ የተራቆተ መሬት በማገገሙ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል። የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በተገቢው ማስረጽ እንደሚገባ ገልጸው ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ስራ በመሳተፍ ኃላፊነቱን እንዲወጣም አሳስበዋል።