ቀጥታ፡
አካባቢ ጥበቃ
ኢትዮጵያ ከካርበን ግብይት መስፈርቶች ጋር የሚጣጣሙ የደን አያያዝ ስራዎችን እያከናወነች ነው
Apr 4, 2026 149
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፍ የካርበን ግብይት መስፈርቶች ጋር የሚጣጣሙ ዘላቂ የመሬትና የደን አስተዳደር ልምዶችን እያሳደገች መሆኑን የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ገለጹ። ዶክተር አደፍርስ ወርቁ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የካርበን ክምችት መኖሩን በማንሳት፤ አብላጫው በደን ሀብት ውስጥ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የደን ሽፋንን ከማሳደግ ባለፈ ሀገሪቱ ከካርበን ሽያጭ የምታገኘው ገቢ እንዲጨምር የጎላ ሚና እየተጫዎተ እንዳለ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በርካታ የብዝሃ ህይወት ባለቤት በመሆኗ የተሻለ የካርበን ክምችት ለመያዝ የሚያስችል ተስማሚ ሥነ-ምህዳር እንዳላት ዶክተር አደፍርስ ገልጸዋል። ሀገሪቱ በአየር ንብረትና በአካባቢ ጥበቃ ስራዎች ላይ በንቃት እየተሳተፈች መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ካርበንን ከአየር ላይ በማስወገድ በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ መንገድ እንዲከማች እያደረገ ነው ብለዋል። ቀደም ሲል በደን መመንጠርና ባልተገባ የመሬት አያያዝ ምክንያት ወደ ህዋ ይለቀቅ የነበረውን ሙቀት አማቂ ጋዝ መከላከል የሚያስችሉ ተግባራት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አማካይነት እየተተገበሩ እንዳለ አስረድተዋል። በዚህም ከካርበን ግብይት መስፈርቶች ጋር የሚጣጣሙ ዘላቂ የመሬት እና የደን አሥተዳደር ልምዶችን ማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙም ገልጸዋል። ሁለተኛው ደግሞ እጽዋት በሚተከሉበት ወቅት ቀደም ሲል ወደ ህዋ የሄደውን ካርበን አምቀው የሚመልሱበትን አሰራር ተግባራዊ በማድረግ እና ከልቀት የተጠበቀውን ካርበን ገበያ ለማቅረብ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ እያከናወነች ባለችው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አማካኝነት የካርበን ሽያጭን ለማጠናከር እየተሰራ መሆኑንና ሀገራት ከኢትዮጵያ ጋር የግዢ ውል ስምምነት እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም የኖርዌይ መንግስት እንደመነሻ የ75 ሚሊዮን ዶላር የካርበን ግዢ እንዲሁም የዓለም ባንክም እንዲሁ የግዢ ውል ማሰሩን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ኖርዌይ እና የዓለም ባንክ ሊገዙት ከሚፈልጉት በላይ ካርበን ማመንጨቷን ጠቁመው፤ እስከ አንድ ቢሊየን ዶላር ሊያመጣ የሚችል ካርበን ሀብት መኖሩን ገልጸዋል። በዓለም ገበያ ላይ ለካርበን ግዢ የሚመደበውን ከፍተኛ ሀብት ወደ ኢትዮጵያ የካርበን ሽያጭ ማምጣት የሚያስችሉ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙም ጠቁመዋል። በዓለም ላይ ያለውን የካርበን ፋይናንስ ወደ ኢትዮጵያ ለማምጣት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ከማጠናከር ባለፈ ሰነዶች የማደራጀትና ሌሎች ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስታውቀዋል።          
ኢትዮ ቴሌኮም ለዲጂታልና ታዳሽ ሃይል ልማት በልዩ ትኩረት እየሰራ ነው
Apr 3, 2026 384
አዳማ ፤መጋቢት 25/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮ ቴሌኮም ዘመናዊ የቴሌኮም አገልግሎትን ከማስፋት ባሻገር ለዲጂታልና የታዳሽ ሃይል ልማት በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን የኩባንያው ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ። ኢትዮ ቴሌኮም በአዳማ ከተማ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ ማዕከል በመገንባት በዛሬው እለት አገልግሎት አስጀምሯል።   በመርሃ ግብሩ ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ፤ በኢትዮጵያ የዲጂታልና የታዳሽ ሃይል ልማት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በአዳማ ከተማ ተገንብቶ በዛሬው እለት ለአገልግሎት ክፍት የተደረገው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ ማዕከልም የዚሁ ልማት ጥረት አካል መሆኑን ጠቁመዋል። የአዳማው ማእከል በአንድ ጊዜ 12 ተሽከርካሪዎችን ቻርጅ የሚያደርግ አቅም እንዳለው ተናግረው በሌሎች አካባቢዎችም የማስፋት እቅድ መኖሩን ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮም ከፈጣንና ዘመናዊ የቴሌኮም አገልግሎት በተጨማሪ ለዲጂታልና የታዳሽ ሃይል ልማት በልዩ ትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።   በዚህም መሰረት አዲስ አበባን ጨምሮ በክልል ከተሞች የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጀ ማድረጊያ ማዕከላትን በማስፋፋት ላይ መሆኑን ገልጸዋል። የአዳማ ከተማ ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ፤ የስማርት አዳማ ፕሮጀክት ተቀርፆ አሰራርና አገልግሎቶችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህ ሂደት የኢትዮ ቴሌኮም አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን አንስተው በከተማዋ ተገንብቶ ለአገልግሎት የበቃው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ ማዕከል ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው አንስተዋል።
በመጪው ሚያዚያ ወር በአብዛኞቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የተሻለ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ ይኖራል
Apr 3, 2026 94
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 25/2018(ኢዜአ)፦ በመጪው ሚያዚያ ወር በአብዛኞቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በመጠንና ሥርጭት የተሻለ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ እንደሚኖር የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፤ ከመጋቢት 23 እስከ ሚያዚያ 22/2018 ዓ.ም የበልግ ዝናብ በመጠንና ስርጭት ከፍተኛ ድርሻ የሚወስድበት ወቅት መሆኑን ገልጿል። በዚህም በመጪው ሚያዚያ ወር በአብዛኛዎቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ከቀደሙት ሁለት የበልግ ወራት በመጠንና ሥርጭት የተሻለ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ እንደሚኖር አስታውቋል። ይህም የአየር ጠባይ ሁኔታ የበልግ አብቃይና ተጠቃሚ አካባቢዎች ለሚያከናውኑት የግብርና ሥራ አመቺ ሁኔታን እንደሚፈጥር ይጠበቃል ብሏል ኢንስቲትዩቱ በመግለጫው። በተለይም በተያዘው የመጋቢት ወር የሚስተዋለው ተከታታይ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ በቡቃያና በተለያየ የዕድገት ደረጃ ላይ ለሚገኙ የበልግ ሰብሎች ምርታማነት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጿል። በደቡብና ደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያ የሚጠበቀው እርጥበታማ የአየር ሁኔታ ለቦረና፣ ጉጂና መሰል ከፊል አርብቶ አደር አካባቢዎች ሰብል ልማት፣ ግጦሽ መሬትና የውሃ አቅርቦት ወሳኝ መሆኑንም አመላክቷል። በዚህም የበልግ አብቃይ አካባቢ አርሶና አርብቶ አደሮች ማሳቸውን በማዘጋጀት የሚጠበቀውን አመቺ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ ለመጠቀም ዝግጅት ማድረግ እንደሚያስፈልግ አሳስቧል። በበልግ ዝናብ መዋዠቅ አዝማሚያ ምክንያት ዝናብ አጠር የሆኑ አካባቢዎች የሚያጋጥማቸውን ተከታታይ ደረቃማ ሁኔታ ለመቋቋም እርጥበትን በማሳ ማቆየት የሚያስችል ስራ ማከናወን እንደሚገባቸውም ኢንስቲትዩቱ አስውገንዝቧል። በሌላ በኩል በአንዳንድ አካባቢዎች በሚኖር ከባድ ዝናብ ሊፈጠር ከሚችል የመሬት መንሸራተት፣ የአፈር መሸርሸርና ቅፅበታዊ የጎርፍ አደጋ ተጋላጭነት ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ አሳስቧል።
የክልሉ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የዜጎችን ተጠቃሚነት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ነው
Apr 3, 2026 98
ባህር ዳር፤ መጋቢት 25/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በለውጡ ዓመታት የተተገበረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የዜጎችን ተጠቃሚነት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከእለት ወደ እለት ስኬታማ እየሆነ መምጣቱ እየተመሰከረለት ነው። በመርሃ ግብሩ በብዛትና እና በአይነት መጠነ ሰፊ ችግኞች ተከላ መካሄዱን ለአካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም፤ ለደን ሽፋን መጨመር ብሎም የምግብ ዋስትን ለማረጋገጥ እያስቻለ ነው። የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ መሰሉ ብርሃኑ ለኢዜአ እንዳሉት፤በለውጡ ዓመታት የተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የዘርፉን ልማት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ነው። መርሃ ግብሩ ለአካባቢ ጥበቃና ለአየር ንብረት ለውጥ መሻሻል፤ ለደን ሽፋን መጨመር እና የምግብ ዋስትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማበርከት ላይ መሆኑንም አስረድተዋል። መርሃ ግብሩ ተግባራዊ መደረጉ በክልሉ 13 ነጥብ 9 በመቶ የነበረውን የደን ሽፋን ወደ 18 ነጥብ 9 በመቶ ለማስደግ እንደተቻለም ነው የተናገሩት። በነዚሁ የለውጥ አመታት በ22 ሺህ 189 ተፋሰሶች ላይ በተካሔደው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ምርታማነት ለማሳደግ ያስቻለ መሆኑንም አብራርተዋል። የአረንጓደ ልማቱ በተለይም ለንብ ማነብ፣ ለእንስሳት እርባታና ለፍራፍሬ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አንስተዋል።  
በአዲስ አበባ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ ተጠናክሮ ቀጥሏል
Apr 2, 2026 124
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ሀገር በቀል እና ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራው ተጠናክሮ መቀጠሉ ተገለጸ፡፡ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እና ዘላቂ የአካባቢ ጥበቃን ለማረጋገጥ፣ የለውጡ መንግስት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን በፖሊሲ ደረጃ ቀርጾ ተግባራዊ በማድረጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ነው፡፡   በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን በመትከል ግቡን እውን ማድረግ ችሏል፡፡ በ2018 ዓ.ም ይህንን ሀገራዊ ስኬት ቀጣይነት ባለው መልኩ ለማከናወን በሀገር አቀፍ ደረጃ 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል። ይህንን ግብ ማሳካት የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በስፋት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በየካ ክፍለ ከተማ የከተማ ውበት እና አረንጓዴ ልማት ጽህፈት ቤት የግብአት አቅርቦትና የችግኝ ጣቢያ ባለሙያ የሆኑት ስንታየሁ ግርማ፤ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል።   በፈረንሳይ የሃ የችግኝ ጣቢያ ለዘንድሮው የክረምት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚውሉ 150ሺህ የሚሆኑ ሀገር በቀል፣ የውበትና የፍራፍሬ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡ እየተዘጋጁ ካሉ የሀገር በቀል የእጽዋት ዝርያዎች መካከል ወይራ እና ብርብራ ተጠቃሽ ሲሆኑ፤ ከፍራፍሬ ዝርያዎች ደግሞ ካዝሚር እና አቮካዶ በስፋት እየተዘጋጁ እንደሚገኙ አብራርተዋል። ይህ የችግኝ ዝግጅት ስራ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የሚደረገውን ጥረት ከመደገፍ ባለፈ፣ ለምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥ የሚውሉ የፍራፍሬ ዝርያዎችን በማካተት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በጣቢያው ለዘንድሮ አረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ለተከላ የሚሆኑ የፍራፍሬና ሀገር በቀል ችግኞችን ጨምሮ ሌሎች ዝርያ ያላቸው ችግኞች እያዘጋጁ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የሶስኒ ችግኝ ጣቢያ አስተባባሪ አበበች መካ ናቸው።   በዚህም በጣቢያው ከ1 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ችግኞች ለማዘጋጀት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው ችግኞች ፍሬያማ እንዲሆኑ ጣቢያው ለችግኞች ተገቢውን እንክብካቤ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማ ውበት እና አረንጓዴ ልማት ቢሮ የአረንጓዴ ቦታዎች አያያዝ፣ ክትትልና ቁጥጥር ዳይሬክተር ሲሳይ አጥናፉ፤ ለዘንድሮው የክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስድስት ሚሊየን ችግኞችን ለማዘጋጀት ታቅዶ በስፋት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።   በመዲናዋ በሚገኙ የችግኝ ጣቢያዎች ለተከላው የሚያስፈልጉ የሀገር በቀል እና የፍራፍሬ ችግኞች በልዩ ትኩረት በማዘጋጀት ላይ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋገረ እና ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለች ሀገርን ለማስተላለፍ የሚያስችል መሠረት የጣለ ታላቅ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው።
የኢትዮጵያ የከተማና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት ስኬቶች በአርዓያነት የሚወሰዱ ናቸው
Apr 2, 2026 142
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የከተማና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ የልማት ስኬቶች የተሻለች አፍሪካን ለመገንባት በአርዓያነት የሚወሰዱ መሆናቸውን የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ጋዜጠኞች ገለጹ። የኢትዮጵያ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስኬቶች በሀገር ገጽታ በመገንባት የከተማ ነዋሪዎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማሻሻል አስተማማኝ ምኅዳር ፈጥረዋል። በአዲስ አበባ ተጀምሮ በበርካታ ከተሞች ተግባራዊ የተደረገው የኮሪደር ልማትም የንግድና ቱሪዝም እንቅስቃሴን በማሳለጥ ዘመናዊ፣ ውብና ፅዱ ከተሞችን እየፈጠረ ይገኛል።   በሌላ መልኩም ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዕድገት ዘላቂነትን ለማረጋገጥ ተግባራዊ ያደረገችው የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ የልማት አቅጣጫም ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው። የአረንጓዴ አሻራና የታዳሽ ኃይል፣ የበጋና የመኸር ወቅት የሰብል ምርታማነት፣ ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄና የአካባቢ ጥበቃ የልማት መርሃ ግብሮች ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ግንባታ አብነቶች ናቸው። በተለይም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ኢትዮጵያን የአፍሪካ ሳንባ የማድረግ ትልም ያስመዘገበው ስኬት የተራቆቱ አካባቢዎችን በደን በመሸፈን ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ ይገኛል።   የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታም አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና እየተቸረው የሚገኝ አስደናቂ የልማት ትልም ሆኗል። የደቡብ ሱዳን፣ ዑጋንዳና ቡሩንዲ ጋዜጠኞች ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ በከተማ ልማትና በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም አስደናቂ የልማት ጉዞ ላይ መሆኗን መስክረዋል። የደቡብ ሱዳን ጋዜጠኛ አይዛክ ዱዶሩ አማኑኤል፤ ለሁለተኛ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ በመጣበት አጋጣሚ አዲስ አበባ የሚታይና የሚጨበጥ የልማት እንቅስቃሴ ያላት ከተማ መሆኗን መገንዘቡን ገልጿል።   ይህም በኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ ፈጣንና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥኑ የልማት መርሃ ግብሮች እየተገነቡ እንደሚገኝ ማሳያ ነው ብሏል። የቡሩንዲ ጋዜጠኛው ሜሻ ኬንዲ ኩምንጋም የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ የልማት መርሃ ግብሮች የተሻለች አፍሪካን ለመገንባት ትምህርት የሚቀሰምበትና አስደናቂ የአመራር ቁርጠኝነት ውጤት መሆኑን ተናግሯል።   የዑጋንዳ ጋዜጠኛ ኮሙ ዴኒስ በበኩሉ፤ የአዲስ አበባ ከተማ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ የልማት መርሃ ግብሮች ጥራትን ከውበት ያሰናሰሉ አስደናቂ የልማት ውጤቶች መሆናቸውን ገልጿል።   የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የታዳሽ ኃይል ልማት መርሃ ግብሮች ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው ዓለም አቀፍ የልማት ውጤቶች እንደሆኑ ተናግሯል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኢኮኖሚ ግንባታም የተሳለጠ ዕድገት የሰፈነባት አፍሪካን እውን ለማድረግ በተሞክሮነት የሚወሰድ መሆኑን አንስቷል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም የአካባቢ መራቆትን በደን በመሸፈን የተፈጥሮ ሚዛንን የሚያስጠብቅ ወሳኝ የልማት እርምጃ መሆኑን አብራርቷል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ ዘርፈ ብዙ ፋይዳዎችን እያበረከተ ነው
Apr 2, 2026 114
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦በሀገራዊ የለውጥ ዓመታት ተግባራዊ የተደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የአፈር ለምነትን በማሳደግና ምርትና ምርታማነትን በማረጋገጥ ረገድ ዘርፈ ብዙ ፋይዳዎችን እያበረከተ መሆኑን የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ ገለፀ። መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ታሪክ ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የተከፈተበትና ሀገራዊ ለውጡ እውን የሆነበት ዕለት ነው፡፡ ይህንኑ ለውጥ ወደ ተግባር ከቀየሩትና የለውጡ ትሩፋት ተብለው ከሚጠቀሱ ስኬቶች መካከል ደግሞ የአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄ በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም. የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር፣ ባለፉት ስድስት ዓመታት የኢትዮጵያን የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ የመቋቋም አቅም ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ትልቅ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው።   የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ዋና ግቡ የሀገሪቱን የደን ሽፋን ማሳደግ፣ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ እና ለቀጣዩ ትውልድ ምቹ አካባቢን መፍጠር መሆኑ ይታወቃል፡፡ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች የተተከሉ ሲሆን የኢትዮጵያን የደን ሽፋን ከ23 ነጥብ 6 በመቶ በላይ ማድረስ ማስቻሉ ከንቅናቄው ስኬቶች መካከል ተጠቃሽ ነው፡፡ የአረንጓዴ አሻራ ሰፊ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታዎች እያስገኘ ሲሆን የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ፣ ከሥራ ዕድል ፈጠራ እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ አድናቆትን ከማስገኘቱም በላይ፣ ለጎረቤት ሀገራትም ችግኞችን በማካፈል ቀጠናዊ ትስስርን ማጠናከር አስችሏል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ መንግስት ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሰጠው ትኩረትም የተፈጥሮ ሃብቶችን በማስጠበቅ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማበርከት ያስቻለ ውጤት ተገኝቷል።   ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል እየተገበረችው ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የአካባቢ ስነ-ምህዳርን በመጠበቅና የደን ሽፋንን በማሳደግ በኩል ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በዚህም በቅርቡ በተለያዩ የአገሪቷ ክፍሎች በተደረገ ጥናት እስካሁን ከተተከለው 48 ቢሊዮን ችግኝ 30 በመቶ የሚሆነውን በአባይ ተፋሰስ የሚገኙ ወረዳዎች ላይ መተከሉን ያሳያል ነው ያሉት። እንዲሁም በአዋሽ ተፋሰስ እና ስምጥ ሸለቆ ውስጥም ተመሳሳይ ጥናት መካሄዱን ገልፀው፤ የመሬቱ የደን ሽፋን በማደጉ የከርሰ ምድር ውሃው በከፍተኛ ሁኔታ መጨመር መቻሉን ጥናቱ ያመለክታል ብለዋል። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት እና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፋኖስ መኮንን በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን የደን ሽፋን በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ እንደሚገኝ ተናግረዋል።   መርሃ ግብሩ ከተጀመረበት ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በተተከለው ችግኝ ተመናምኖ የነበረው የደን ሽፋን ከጊዜ ወደ ጊዜ እንዲሻሻል አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። በዚህም አሁን ላይ የደን ሽፋኑን ከ17 ነጥብ 2 በመቶ ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ማድረግ መቻሉን ባለፈው ዓመት የተደረገ ጥናት እንደሚያሳይም ጠቅሰዋል። መርሀ-ግብሩ በኢትዮጵያ ያለውን የደን ሽፋን በእጅጉ ከማሳደጉ ባሻገር በአትክልትና ፍራፍሬ ምርትና ምርታማነት በመጨመር ከህዝቡ ተጠቃሚነት ባሻገር ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሪ እያስገኘ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት በምርምር ማገዝ ይገባል
Mar 31, 2026 146
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በምርምርና በሳይንስ ማገዝ እንዳለባቸው የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለፁ። የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎች የአየር ንብረት ትግበራ ፎረም የመጀመሪያ ጠቅላላ ጉባኤ እየተካሄደ ነው። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት፤ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በሚደረገው ብሔራዊ ጥረት ሊኖራቸው የሚገባውን ስትራቴጂያዊ ሚና አፅንኦት ሰጥተው ተናግረዋል።   ሳይንሳዊ የመፍትሄ ሃሳቦችን በማፍለቅ በኩል በቅንጅት መስራት እንደሚጠበቅባቸውም አቶ ስዩም አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመመከት በአየር ንብረት የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂን በመተግበር ቀዳሚ መሆኗን ጠቁመዋል። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን መትከል እና በታዳሽ ኃይል ልማት የተመዘገቡት ስኬቶች ኢትዮጵያ ለአፍሪካና ለዓለም አርአያ መሆኗን የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል። ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጥናትና ምርምር ስራዎቻቸው፣ የድህረ-ምረቃ ተማሪዎች የመመረቂያ ጽሁፎችንና ጆርናሎቻቸውን በአየር ንብረት ለውጥና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ መሆን አለባቸው ብለዋል። ፎረሙ የፖሊሲ አውጪውንና የትምህርት ተቋማቱን የተቀናጀ ስራ የሚያጠናክር መድረክ እንደሆነም ጨምረው ገልጸዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአየር ንብረት ጉዳዮችን በበላይነት እንደሚመራ ተቋም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር የጀመረውን ቅንጅት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።   የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ክፍሌ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲዎች የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ ሳይንሳዊ መፍትሄዎችን በማፍለቅ በኩል ከፍተኛ ሚና አላቸው። እንደሀገር እየተተገበረ ባለው የአረንጓዴ አሻራ ልማት እና የአየር ንብረት መቋቋም አቅም ግንባታ ስራዎች ላይ የዩኒቨርሲቲዎች ተሳትፎ ከንድፈ ሀሳብ ወደ ተግባር የተሻገረ መሆን እንዳለበትም ተናግረዋል። የፎረሙ መመስረት ለአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄ ፍለጋ ትልቅ ምዕራፍ መሆኑን ገልጸው እንደሀገር የተጀመሩ ሥራዎችን መደገፍ የሚያስችል ነው ብለዋል።
በዞኑ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ ለመስኖ ልማት መስፋፋት አመቺ ሁኔታን ፈጥሯል
Mar 30, 2026 145
ጎንደር መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ) :-በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተካሄደው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት ስራ የከርሰ ምድር ውሃ አቅርቦትን በማሻሻል ለበጋ መስኖ ልማት መስፋፋት አመቺ ሁኔታ መፍጠሩን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ በአማራ ክልል የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራው ከ2003 ዓ/ም ጀምሮ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ይገልፃል። የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃውም የአፈር ክለትን በመቀነስ ውሃማ አካላትና የመስኖ መሰረተ ልማት በደለል እንዳይሞሉ በማድረግ የሰብል፣ የእንስሳትና ፍራፍሬ ምርታማነትን ለማሳደግ አስተዋፅኦ እያደረገ ይገኛል። የመምሪያው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ ለኢዜአ እንደገለጹት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት የለም አፈር መከላትን በማስቀረት ለሰብል ምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። ይህም የከርሰና ገጸ ምድር ውሃ አቅም እንዲጨምር በማድረግ አርሶ አደሩ በዓመት እስከ ሶስት ጊዜ በመስኖ በማምረት የምግብ ሉዓላዊነቱን ለማረጋገጥ እየረዳው መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ ከአምስት ሄክታር በታች የነበረውን ዓመታዊ የመስኖ ልማት ስራ አሁን ላይ ወደ 40 ሺህ ሄክታር መሬት በመስኖ እንዲለማ የሚያስችል ውጤት ማስገኘቱን አስረድተዋል፡፡ በዞኑ ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተጠብቀው እየለሙ የሚገኙ ተፋሰሶች ቁጥር 955 መድረሱን ጠቁመው ይህም የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብሩ እንዲሳካ ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ብለዋል። አሁን ላይ በንብ ማነብ፣ በእንስሳት ማድለብና በወተት ላሞች እርባታ ለተሰማሩ 1 ሺህ 350 ወጣቶች የስራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማስቻሉን ተናግረዋል፡፡ በዘንድሮ በጋም በድግግሞሽ ከ11 ሚሊዮን በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች ባካሄዱት የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ 57 ሺህ 370 ሄክታር የተራቆተ መሬት ላይ የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ማከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ የጎንደር ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ሰጠኝ አለነ እንደገለጹት በበጋው የምናከናውነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት ስራ በመስኖ፣ በእንስሳትና በሰብል ልማት ምርታማነታቸው እንዲያድግ አስችሏል። በበጋ መስኖ በመታገዝ በአንድ ሄክታር መሬታቸው ላይ ቲማቲም፣ ሽንኩርትና ጥቅል ጎመን አምርተው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ያስቻላቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የጭልጋ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር እሱባለው መሳፍንት በበኩላቸው በለሙ ተፋሰሶች ላይ በ15 ዘመናዊ የንብ ቀፎዎች ታግዘው ማር አምርተው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የህልውናችን መሰረት መሆኑን በመገንዘባችን በልማት ቡድኖች ተደራጅተን በየዓመቱ በግልና በወል መሬቶች ላይ የእርከንና ክትር ስራዎችን እያከናወንን እንገኛለን ብለዋል፡፡  
የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ የብዝኃ ሕይወት ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውል ያስችላል
Mar 29, 2026 261
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፡- የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ኢትዮጵያ ያላትን ዕምቅ የብዝኃ ሕይወት ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል ገንቢ ሚና እንዳለው የዘርፉ ምሁራን ገለጹ፡፡ በአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የአካባቢ ሕጎችና ደረጃዎች ዴስክ ኃላፊ ወንደሰን ታደሰ፤ ኢትዮጵያ የውኃ፣ የደን፣ የዓየር ንብረት አገልግሎት፣ የቁጥጥርና ቱሪዝም ሥርዓተ-ምኅዳር ብትታደልም በሚገባት ልክ አልተጠቀመችም ብለዋል።   የሥርዓተ-ምኅዳር ጉዳዮች በሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ ጉዳዮች በከፍተኛ ጫና ላይ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።   የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ በአገልግሎቱ አቅራቢዎችና ተጠቃሚዎች መካከል የጋራ መግባባትን በመፍጠር ዘላቂ የአካባቢ ጥበቃ ሥርዓትን ማጠናከር እንደሚያስችልም አስረድተዋል። የፋርም አፍሪካ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ሸዊት አማኑኤል በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያን የብዝኃ ሕይወት ሃብቶች ለሕብረተሰቡ ይበልጥ ጥቅም ላይ እንዲውሉ የሚያስችል ሥራ እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ የባሌ አካባቢ ማኅበረሰብ ተፈጥሮን በመንከባከብ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ተጠቃሚ መሆን መጀመሩን ገልጸው፤ ይህ በሁሉም አካባቢዎች መስፋት እንዳለበት አመላክተዋል። መንግሥት በአረንጓዴ ዐሻራና በአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ማስመዝገቡን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ ያላትን የብዝኃ ሕይወት ሀብት ይበልጥ መለየትና ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡   በመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የውኃ ሀብትና ሀይድሮሎጂ መምህር ዓለምአየሁ አባተ (ዶ/ር)፤ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ማኅበረሰቡ የሠራበትን እንዲያገኝ በማድረግ የተጠናከረ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ማከናወን ያስችላል ብለዋል፡፡ በባሌ ኢኮሎጂ በ20 ወረዳዎች በመሰማራት እየሠሩ መሆኑን የገለጹት የፋርም አፍሪካ ፕሮግራም ሥራ አስኪያጅ ፈይሳ አሰፋ፤ በኢትዮጵያ የካርበን ክፍያ መጀመሩ የሕብረተሰቡን የአካባቢ ጥበቃ ተነሳሽነት ያሳድጋል ብለዋል፡፡ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጁ ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የብዝኃ ሕይወት ሀብት ጠብቃ እንድትቆይና ማኅበረሰቡ ተገቢውን ጥቅም እንዲያገኝ ያስችላል ሲሉም አስገንዝበዋል።
በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ ነው
Mar 28, 2026 163
አምቦ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በጽህፈት ቤት የደን ልማት ባለሙያ ጉደታ ጡሪ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ እየተዘጋጁ ከሚገኙ ችግኞች መካከል ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ዝርያዎች እንደሚገኙበት ተናግረዋል። በክረምቱ ወራት አጠቃላይ ከ94 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የችግኝ ተከላ እንደሚከናወን ገልጸው፤ የችግኝ ማፍላት ስራው በዞኑ በሚገኙ ሁሉም ወረዳዎች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ባሳተፈ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ዝግጅቱ የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንዲቻል ምርታማነታቸው ከፍተኛ በሆኑና በተሻሻሉ የችግኝ ዝርያዎች ላይ ትኩረት ማድረጉንም ጠቅሰዋል። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሮች አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተው፤ ችግኞችን የመንከባከብና የመጠበቅ ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑንም አክለዋል። የተተከሉ ችግኞች የአካባቢ ስነ-ምህዳርን ከመቀየር አንጻር ከፍተኛ ሚና ከመጫወታቸው ባለፈ፣ ደርቀው የነበሩ ኩሬዎች ዳግም ውሃ እንዲይዙ በማድረግ ለአርሶ አደሩ ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል ነው ያሉት። ባለፉት ሰባት ዓመታት በድምሩ 616 ሺህ 613 ሄክታር መሬት ላይ ችግኞች መተከላቸውን አስታውሰው፤ የአካባቢው ማህበረሰብ ያለውን ደን የመጠበቅ ባህላዊ እሴት ለአረንጓዴ ልማት ስራው ስኬታማነት ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን ገልጸዋል።
ለቀጣዩ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ ነው    
Mar 27, 2026 146
ሆሳዕና፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ ሻራ መርሐ-ግብር የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ደንና አካባቢ ጥበቃ ልማት ቢሮ አስታውቋል።   የቢሮው ኃላፊ አብርሃም መጫ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ባለፉት 7 ዓመታት በክልሉ 450 ሺህ ሔክታር በአካባቢ ጥበቃና በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ማልማት ተችሏል።   በዚህም የአፈር ለምነትን በማስጠበቅ፣ የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥን ጨምሮ በበርካታ ዘርፎች ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን አብራርተዋል። በዚህ ዓመትም 270 ሚሊየን የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች በመትከል 80 ሺህ ሔክታር መሬትን ለማልማት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሠራን ነው ብለዋል። ሥነ-ምኅዳርን መሠረት ያደረጉ ለምግብነትና ለሌሎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የሚውሉ ችግኞችን የማፍላትና የማዘጋጀቱ ተግባር እየተከናወነ እንደሚገኝም ነው ያረጋገጡት።
የበልግ ዝናብ ስርጭት ለግብርና ምርታማነትና ለእንስሳት መኖ አቅርቦት ከፍተኛ ፋይዳ ያለው ነው-የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት
Mar 26, 2026 252
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018(ኢዜአ)፦የዘንድሮው የበልግ ዝናብ ስርጭት በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ለሚከናወኑ የግብርና ስራዎች ስኬታማነትና ለእንስሳት መኖ አቅርቦት መሻሻል ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢንስቲትዩቱ የትንበያ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አሳምነው ተሾመ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ፤ ተቋሙ የአየር ጸባይ አዝማሚያዎችን፣አዎንታዊና አሉታዊ ተጽዕኖዎችን በወቅቱ ለማህበረሰቡና ለሚመለከታቸው ተቋማት የማድረስ ስራውን በልዩ ትኩረት እየከወነ ይገኛል። ከየካቲት እስከ ግንቦት ባለው የበልግ ወቅትም፣ በተለይም በሀገሪቱ ደቡባዊ አጋማሽ የዓመታዊ ዝናብ መጠኑ እስከ 55 በመቶ የሚሸፈንበት ዋነኛ ወቅት ነው ብለዋል። በ2018 ዓ.ም የበልግ ወቅት አብዛኞቹ የአገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ እንደሚያገኙ ተናግረዋል፡፡ እስካሁንም በ55 የሚደርሱ አካባቢዎች በ24 ሰዓት ውስጥ ከ35 እስከ 148 ሚሊ ሜትር የሚደርስ ከፍተኛ መጠን ያለው ዝናብ መመዝገቡን ገልጸዋል። ባለፉት ቀናት የታየው ተስፋ ሰጪ የዝናብ ስርጭት ለአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች እንዳሉት ጠቅሰው፥ ለበልግ እርሻ ዝግጅትና ለዘር ስራ ምቹ ሁኔታን መፍጠሩንም ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ለሰውና ለእንስሳት የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ማሻሻሉን እንዲሁም የእንስሳት መኖ ልማትን በማፋጠን ረገድ ከፍተኛ ድርሻ መኖሩ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። በመጪዎቹ ሚያዝያና ግንቦት ወራትም በደቡብ፣ በደቡብ ምዕራብ፣ በመካከለኛውና በሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች የበልግ ዝናብ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በተለይም በደቡብና በደቡብ ምዕራብ አካባቢዎች ዝናቡ ዘግይቶ የሚወጣ በመሆኑ ለግብርናውና ለአካባቢ ጥበቃ ስራው ተጨማሪ ዕድል እንደሚፈጥር አስረድተዋል። ይሁን እንጂ፣ ከፍተኛ መጠን ያለው ዝናብ ወደ ጎርፍ አደጋ ሊቀየር ስለሚችል ማህበረሰቡና የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል።
በጣና ሐይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም ለማጥፋት አዲስ የንቅናቄ ዘመቻ ተጀመረ
Mar 25, 2026 155
ባህር ዳር ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ በጣና ሐይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም ለማጥፋት አዲስ የንቅናቄ ዘመቻ ተጀመረ። የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በሐይቁ ህልውና ላይ አደጋ የደቀነውን የእምቦጭ አረም በተደመረ አቅም ለማስወገድ የትብብር ጥሪ አቅርቧል። ከጣና ሃይቅና አካባቢው የእምቦጭ አረምን ለማስወገድ የሚያስችል የንቅናቄ መርሃ ግብር በባህር ዳር ከተማ ሽንብጥ ቀበሌ የጣና ዳርቻ በዛሬው እለት በይፋ ተጀምሯል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ሃላፊ አቶ ተስፋሁን አለምነህ፤ በጣና ሃይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም በተባበረ ክንድ በማስወገድ የሃይቁን ህልውና መጠበቅ ይገባናል ብለዋል።   አረሙን ለማጥፋት በሰው ኃይል እና በማሽን እንዲሁም አጠቃላይ የሕዝቡን ጠንካራ ተሳትፎ ማእከል ያደረገ ስራ የሚጠይቅ መሆኑን ገልጸዋል። የእምቦጭ አረም በቀላሉ የመስፋፋትና የማንሰራራት ባሕሪ ያለው በመሆኑ ቀጣይነት ያለው ዘመቻ እና የክትትል ስራ የሚያስፈልግ ስለመሆኑም አፅኖት ሰጥተዋል። በመሆኑም በሐይቁ ህልውና ላይ አደጋ የደቀነውን የእምቦጭ አረም በተደመረ አቅም ለማስወገድ እንዘጋጅ በማለት ኃላፊው ጥሪ አቅርበዋል። የመከላከል ሥራው በሰው ኃይልና በማሽነሪ በመታገዝ እንዲሁም ከባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በባዮሎጂካል ዘዴ እየተከናወነ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።
ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ማሳካት በሚያስችል መልኩ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Mar 25, 2026 156
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ በ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ማሳካት በሚያስችል መልኩ ውጤታማ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ(ዶ/ር) ገለጹ። አስተባባሪው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ዘንድሮ የሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር፣ የመጀመርያው ምዕራፍ ማጠቃለያ ዓመት በመሆኑ ዝግጅቱ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡ በዚህም በዘንድሮው መርሃ-ግብር በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ በላይ ለመትከል እቅድ ተይዞ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት የተገኙ ተሞክሮዎችን በማስፋት የፍራፍሬ ችግኞችን የማስፋት፣ የሀገር በቀል ዝርያዎችን ቁጥር ከፍ የማድረግ ብሎም የእፅዋት አይነት ስብጥር በሰፊው እየተሰራበት መሆኑንም ገልፀዋል። በበጋው ወቅት የተከላ ቦታዎችን የመለየት፣ የተለዩ ቦታዎች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ የማከናወን፣ ከየአካባቢው አየር ንብረት ጋር የሚጣጣሙ ችግኞችን የማፍላትና የተለዩ ቦታዎች ላይ ካርታ የማዘጋጀት ስራ በስፋት መከናወኑን ነው ያስታወቁት።   በዚህም በክልሎች እስካሁን 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ሄክታር መሬት ለችግኝ ተከላ የሚውሉ ቦታዎችን መለየታቸውን ጠቅሰው እስካሁን ከ110 ሺህ በላይ ችግኝ ጣቢያዎች ወደ ስራ ገብተው ችግኞች እያፈሉ ይገኛሉ ብለዋል። በዘንድሮው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ7 ነጥብ 5 ቢሊየን በላይ ችግኝ ለመትከል በእቅድ መያዙን ተናግረው እስካሁን 6 ነጥብ 1 ቢሊየን ችግኝ ዝግጁ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ በቀሪው ጊዜ የእንክብካቤ ተግባራት እንደሚከናወኑ ጠቅሰው ጉድጓድ የማዘጋጀት ስራዎችን ጨምሮ ሌሎችም እንደሚከናወኑ ገልጸዋል፡፡ ቀደም ሲል የነበረውን የክረምት ዝናብ ብቻ የመጠበቅ ልምድ መቀየሩን ጠቁመው ይህም ችግኞች ረጅም የዝናብ ወቅት እንዲያገኙ በማድረግ የፅድቀት መጠናቸውን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚጨምረው አስረድተዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አሁን ላይ የህዝቡ ባህል እየሆነ መምጣቱን ጠቅሰው በቀጣይም የዜጎችን የባለቤትነት ስሜት የማሳደግ እና የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
በክልሉ ከ458 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ተከናውኗል-ቢሮው
Mar 24, 2026 156
‎ባህርዳር ፤መጋቢት 15 /2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በዘንድሮው የበጋ ወራት በአርሶ አደሩ ተሳትፎ በ458 ሺህ 794 ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ መከናወኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ ። ‎የቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንደገለፁት በክልሉ በዘንድሮ ‎የበጋ ወራት ከዘጠኝ ሺህ የሚበልጡ ተፋሰሶችን መሰረት ያደረገ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ ተካሂዷል። በዚህም ከ458 ሺህ 794 ሄክታር በላይ መሬት ላይ የማሳና የጋራ ላይ ዕርከን ስራዎችን መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። ‎እንዲሁም ‎ከ91 ሺህ ሄክታር በላይ የተራቆቱና የተጎዱ ተራራማ ቦታዎችን በመከለል ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተጠብቀው መልሰው እንዲያገግሙ መደረጉንም አመልክተዋል ። በተጨማሪም ‎ከ7 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚበልጡ የተለያዩ የውሃ ማስረጊያ ስትራክቸሮች መከናወናቸውን ጠቁመው የውሃ ማፋሰሻና መቀልበሻ ቦዮች ግንባታ ስራዎችም መካሄዳቸውን ተናግረዋል ። አርሶ አደሩ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ የህልውና ጉዳይ መሆኑን በየጊዜው እየተረዳ በመምጣቱ ከዕቅድ በላይ ስራውን መፈፀም እንደተቻለም አስታውቀዋል። ‎በመጭው የክረምት ወቅት ‎በበጋ ወራት የተከናወነውን የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ በስነ-ህይወታዊ ዘዴ ለማጠናከር ከወዲሁ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አመላክተዋል። ‎በምዕራብ ጎጃም ዞን የሰከላ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ዓለሙ ይግዛው እንዳሉት የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ መስራት ከተጀመረ ወዲህ የተራቆቱ መሬቶች ደን መልበስ ጀምረዋል ። ‎የእርሻ መሬቶችም የአፈር ለምነታቸው እንዲጨምርና የሰብል ምርታማነት እየተሻሻለ እንዲመጣ ማስቻሉንም ገልፀዋል። ‎‎የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ የህልውና ጉዳይ በመሆኑ በየዓመቱ እየሰራን እንገኛለን ያሉት ደግሞ በአዊ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን የጓንጓ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሙሉነህ ይግዛው ናቸው። ‎ባለፉት ዓመታት በሰራነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ተፋሰሶች በማገገማቸው ለእንስሳት ዋነኛ የመኖ ምንጭ ሆነዋል ብለዋል።  
የሚቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎትን በማዘመን የሚኖረውን ጠቀሜታ ለማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Mar 23, 2026 199
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦የሜቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎትን ዘመናዊና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለማድረግ የጀመራቸውን ስራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የተፈጥሮ ሃብት አገልግሎት አቅራቢዎች ለሥነ-ምኅዳር ደኅንነት በይበልጥ ሊተጉ ይገባል ኢንስቲትዩቱ ዓለም አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ ቀንን በኢትዮጵያ ለ45ኛ ጊዜ "ዛሬን መመልከት ፤ነገን ለመጠበቅ " በሚል መሪ ሀሳብ እያከበረ ይገኛል።   የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተርና በዓለም አቀፉ የሚቲዎሮሎጂ ድርጅት የአፍሪካ አህጉር ፅህፈት ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ፈጠነ ተሾመ እንደገለጹት፤ የአየር ንብረት ለውጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት ላይ አሉታዊ ተፅእኖ እያሳደረ ያለ ጉዳይ ነው። በመሆኑም ተፅእኖውን መግታት የሚያስችል የሚቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎት አሰጣጥን ማጠናከር ዋነኛው ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ እያስመዘገበች ያለውን ፈጣን እድገት ለማስቀጠል የሚቲዎሮሎጂ መረጃ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ኢኒስቲትዩቱ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል አቅም መገንባት ላይ በትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በተለይም አጋር አካላትን ባሳተፈ መልኩ ተጨማሪ አቅም የሚፈጥሩ መሰረተ ልማቶችን ማስፋፋት፣ዘመኑን የዋጁ ቴክኖሎጂዎችን ጥቅም ላይ ማዋል እና የሰው ሀይል ልማት ዋና ዋናዎቹ ስለመሆናቸው አንስተዋል።   በኢትዮጵያ ለ45ኛ ጊዜ የሚከበረው ዓለም አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ ቀን ስራዎችን ይበልጥ ለማጠናከርና ተደራሽነትን ለማስፋት አስቻይ ሁኔታ እንደሚፈጥር አክለዋል። በተጨማሪም ኢንስቲትዩቱ የሚሰጠውን አገልግሎት በዘመናዊ የሚቲዎሮሎጂ ሳይንስ ላይ በመመስረት ዛሬ የተሻለ መረጃ በመያዝ የተሻለ ነገን ለመገንባት የተለያዩ የጥናትና ምርምር ስራዎችን እየሰራ ስለመሆኑን ገልጸዋል።
የትራንስፖርት ዘርፉን ከአካባቢ ብክለት የጸዳ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል
Mar 23, 2026 186
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የትራንስፖርት ዘርፉን ከአካባቢ ብክለት የጸዳ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሐሰን ገለጹ፡፡ በባህር ዳር የአውሮፕላን ማረፊያ ማስፋፊያን ጨምሮ ግዙፍ መሠረተ ልማቶች ግንባታ እየተፋጠነ ነው ኢትዮጵያ በትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ መሰረተ ልማት፣በከተማ ትራንስፖርት እና አረንጓዴ ቴክኖሎጂዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ዘላቂ የትራንስፖርት ስርዓት ለመዘርጋት እየሰራች ትገኛለች። ይህንን ለመደገፍ ታዳሽ የኃይል ምንጭ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን ማስፋፋትና ዘርፉን ማበረታታት ከተሽከርካሪ የሚለቀቀውን በካይ ጋዝ ለመቀነስ ያስችላል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሐሰን ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ዘርፉ አካባቢን እንዳይበክል ከማድረግ አኳያ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል፡፡ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለሚያስመጡና ለሚገጣጥሙ አካላት አተገባበርን በተመለከተ ፖሊሲ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እየተደረገ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ በዚህ ከቀረጥ ነጻን ጨምሮ ልዩ ልዩ ማበረታቻዎች እየተደረገላቸው መሆኑን አንስተዋል፡፡ በነዳጅ የሚሰሩ ከሁለት እግር እስከ የከተማ ባስ እና የጭነት ተሽከርካሪዎች ድረስ ወደ ሀገር እንዳይገቡ ክልከላ መደረጉንም ተናግረዋል፡፡ ይህ እርምጃ ኢትዮጵያ ለዓለም የአየር ንብረት መጠበቅ ያላትን ቁርጠኝነት ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡ በአስር ዓመቱ ስትራቴጂ የልማት እቅድ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ500 ሺህ በላይ ተሽካርካሪዎች የታዳሽ ኃይል አማራጭን እንዲጠቀሙ ለማድረግ ታስቦ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ታዳሽ የኃይል አማራጭን የሚጠቀሙ የተሽከርካሪዎች ቁጥር 115 ሺህ መድረሱን ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የትራንስፖርት ዘርፉን ከአካባቢ ብክለት የጸዳ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን አመላክተዋል፡፡ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ፖሊሲ የትራንስፖርት ዘርፉ አካባቢን እንዳይበክል ከማድረግ ባሻገር ታዳሽ የኃይል አማራጭ ላይ ትኩረት እንዲደረግ እና የነዳጅ ጥገኝነትን ለመቀነስ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ እንደ የነፋስ ኃይል፣ የኃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ የተፈጥሮ ጋዝ እና ሌሎች የታዳሽ ኃይል አማራጮች በስፋት መገኘት ከነዳጅ ተሽከርካሪዎች ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚደረገውን ሽግግር አስተማማኝ እንዳደረገው ጠቁመዋል፡፡
የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው - አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ
Mar 21, 2026 166
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሌሎች ሀገራት ትልቅ መነሳሳትን የሚፈጥርና ምሳሌ የሚሆን ፕሮጀክት ነው ሲሉ በኢትዮጵያ የኮሎምቢያ አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተጀመረው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እስካሁን ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ተተክለዋል። ይህም የአካባቢ ጥበቃን ከማጠናከር ባለፈ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ብዝሃ ህይወትን ለመጠበቅ ትልቅ ሚና እየተጫወተ ነው። ይህ መርሃ ግብር በአፍሪካ ቀዳሚ የሆነ ግዙፍ የደን ልማትና የተፈጥሮ ጥበቃ ዘመቻ ሲሆን የካርቦን ልቀትን በመቀነስ ረገድም በምሳሌነት ተጠቃሽ ነው። ሀገሪቱ የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም የተፈጥሮ ሥርዓት እንድትገነባ እያገዘም ይገኛል።   በኢትዮጵያ የኮሎምቢያ አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ ለኢዜአ በሰጡት ቃለ ምልልስ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሚመራው የአረንጓዴ አሻራ ፖሊሲ እጅግ የሚደነቅ ጥረት ነው ብለዋል። አረንጓዴ አሻራ ለሌሎች ሀገራትና መሪዎች አርአያ የሚሆን ተሞክሮ እንደሚሆን ጠቁመው ይህ ተግባር ሁላችንም በጋራ እንድንሰራ ያበረታታናል ነው ያሉት። የሀገራት መሪዎች በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት እየመጡ ያሉ ተግዳሮቶችን ለዜጎች በግልጽ ማሳወቅ እንዳለባቸውና ይህም ዜጎች ለመፍትሄው እንዲሰሩ ያደርጋል ሲሉ ገልጸዋል። በተጨማሪም ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2027 የሚካሄደውን 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 32) እንድታስተናግድ መመረጧን አምባሳደሩ አድንቀዋል። ኮሎምቢያ እ.ኤ.አ. በ2024 የኮፕ 16 ጉባኤን ማስተናገዷን አውስተው ኢትዮጵያ ኮፕ 32ን በምታዘጋጅበት ወቅት ሀገራቸው ያካበተችውን ልምድ ለማካፈል ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል። አምባሳደሩ አክለውም የኮሎምቢያን ተሞክሮና የኢትዮጵያን የወደፊት ራዕይ በማጣመር፣ ተግዳሮቶችን በጋራ ለመፍታት ይሰራሉ ብለዋል።
የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ለሚያሻሽሉ መመሪያዎች ተፈፃሚነት ጥብቅ ቁጥጥር ይደረጋል
Mar 21, 2026 173
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ የሚያሻሽሉ መመሪያዎችን በማውጣት ለተግባራዊነታቸው ጥብቅ ቁጥጥር እንደሚደረግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢዎችና የአካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ከፋርም አፍሪካና ኤስ.ኦ.ኤስ ሳህል ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በሥርዓተ ምህዳር አገልግሎት ክፍያ ትግበራ ላይ ትኩረት ያደረገ የውይይት መድረክ አካሂዷል፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የባለድርሻ ተቋማትን ትብብር በማጠናከር በደንብ ቁጥር 545/2016 በተሰጠው ኃላፊነት መሰረት የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ሥርዓትን ይከታተላል፤ ይቆጣጠራል፡፡ የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ተፈጥሮ የቸራትን ዕምቅ የብዝኅ ህይወት ሃብት በሚገባት ልክ ጥቅም ላይ እያዋለች እንዳልሆነ ገልጸዋል። ለዚህም የውሃና የየብስ የሥነ-ምኅዳር ጸጋዎች ለሀገር የኢኮኖሚ ጥቅም ለማዋል የሚስችል "የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ቁጥር 140/2018" ተግባራዊ መደረጉን አስታውቀዋል። ምክር ቤቱም ከመንግስተና የዘርፉ ተዋናዮች ጋር የግብዓት ማሰባሰቢያ መድረኮችን በማዘጋጀት ግብዓት ታክሎበት አዋጁን በማፅደቅ ሥራ ላይ እንዲውል መደረጉን ተናግረዋል። በዚህም የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ለማሻሻል የሚረዱ የማስፈጸሚያ ደንቦችና መመሪያዎች መውጣታቸውንና ተፈፃሚነ መሆናቸውን ጥብቅ ክትትል እንደሚደረግ አንስተዋል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ንጉሱ ለማ፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተቀናጀ የሥነ-ምህዳር አገልግሎት የክፍያና የሕግ ማዕቀፍ እንዳለነበረ ገልጸዋል፡፡ በዚህም የኢትዮጵያ ሥርዓተ ምኅዳር ዘላቂነት ለማስጠበቅ የመንግስትና የባለድርሻ ተቋማትን ፍላጎት ታሳቢ ያደረገ የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ቁጥር 140/2018 መፅደቁን ተናግረዋል። የአገልግሎት ክፍያ የአሰራር ሥርዓቱም የኢኮኖሚ ዕድልን በመፍጠርና ለአገልግሎቱ አቅራቢዎች ዘላቂ ዋስትናን ይፈጥራል ብለዋል፡፡ አዋጁን መነሻ በማድረግ የዘርፉን ተዋናዮች ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል የማስተግበሪያ መመሪያ መዘጋጀቱን አስረድተዋል። የፋርም አፍሪካ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ሸዊት አማኑኤል፤ ኢትዮጵያ ደኖችን በመንከባከብ የበካይ ጋዝ ልቀትን በመቀነስ ለዓለም የከባቢ አየር ሥነ ምህዳር ገንቢ ሚና እየተወጣች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያዊያን ደንን በመንከባከብ በአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ በሚበረክቱት አስተዋፅኦ ልክ ሳይንሳዊ ጥናትና ኦዲት ተካሂዶ ገቢ ማመንጨት መጀመሩን አንስተዋል። የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ በባሌ አካባቢ የተጀመረውን በሌሎች አካባቢዎች ለማስፋት በር የሚከፍት መልካመ ዕድል መሆኑንም ተናግረዋል፡፡  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም