ቀጥታ፡
አካባቢ ጥበቃ
የአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ትንበያ ፎረም በአዲስ አበባ ይካሄዳል
May 11, 2026 165
አዲስ አበባ፤ግንቦት 3/2018 (ኢዜአ)፡-73ኛው የታላቁ የአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ትንበያ ፎረም (GHACOF 73) ግንቦት 10 እና 11 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይደረጋል። ፎረሙ የሚካሄደው “የአየር ንብረት አገልግሎቶች፤ ለአይበገሬነት እና ዘላቂ ልማት” በሚል መሪ ሀሳብ ነው። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) የአየር ንብረት ትንበያ እና የመተግበሪያ ማዕከል(ICPAC) ከልማት አጋሮች ጋር በመሆን ፎረሙን እንዳዘጋጀው ተገልጿል። ስብሰባው ትንበያ ከመስጠት ባለፈ ትንበያዎቹን ወደ ተግባር መቀየር እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የቅድመ ማስጠንቀቂያና ቅድመ ዝግጅት እርምጃዎችን ማጠናከርን ያለመ ነው። የአየር ንብረት መረጃዎች አርሶ አደሮች ፣ የጤና ባለሙያዎችን እና የአደጋ ስጋት አመራሮችን በቀጥታ እንዲደግፉ ማድረግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ምክክር እንደሚደረግ ኢጋድ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል። በብሔራዊ የሚቲዎሮሎጂ ተቋማት መካከል ያለውን ትብብር ማጠናከር ሌላኛው የመወያያ አጀንዳ ነው። መድረኩ ለታላቁ የአፍሪካ ቀንድ ግብርና እና የውሃ ሀብት ወሳኝ የሆነውን ከእ.አ.አ ከጁን እስከ ሴፕቴምበር 2026 ያለውን የዝናብ ወቅት ትንበያ ይቀርብበታል። ሚኒስትሮች፣ የምርምር ተቋማት፣ ሰብአዊ ድርጅቶች፣ የሲቪክ ማህበራት እና የግል ባለሀብቶች ይሳተፋሉ።ይህ የተሳታፊዎች ስብጥር ሳይንስን ከፖሊሲ ጋር ለማገናኘት የታለመ ነው። የአየር ንብረት መዛባት የሩቅ ስጋት መሆኑ ቀርቶ በደጃፋችን ላይ ያለ ተጨባጭ አደጋ ነው ያለው ኢጋድ ፎረሙ በታላቁ የአፍሪካ ቀንድ የሚገኙ ማህበረሰቦች በቂ መረጃ እንዲኖራቸውና አስቀድመው ዝግጁ እንዲሆኑ ማስቻል ላይ ትኩረቱን ያደረገ መሆኑን አመልክቷል።
የኢትዮጵያ የተፋሰስና የአካባቢ ጥበቃ ስኬታማ የልማት መርሃ ግብሮች የበለፀገ የደን ሃብት እንዲፈጠር እያደረገ ነው
May 9, 2026 303
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 1/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የተፋሰስና የአካባቢ ጥበቃ ስኬታማ የልማት መርሃ ግብሮች የበለፀገ የደን ሃብት እንዲፈጠር እያደረገ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። በተያዘው በጀት ዓመት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት መርሃ ግብር 3 ነጥብ 9 ሚሊየን ሄክታር መሬት መልማቱንም አስታውቋል። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈፃሚ ፋኖሴ መኮንን፤ የሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋ የፈጠረው የደን መመናመን ከፍተኛ የአካባቢ መራቆትን አስከትሎ ነበር ብለዋል። ይህም የኢትዮጵያ የአፈር ለምነትን በመቀነስ በግብርና ምርታማነት፣ በዱር እንስሳትና ዕፅዋት ደኅንነት ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ ፈጥሮ እንደነበር አስታውሰዋል። በዚህም በኢትዮጵያ ሀገራዊ ለውጥ ማግስት በአረንጓዴ አሻራና የአካባቢ ጥበቃ ልማት መርሃ ግብር የሥነ-ምኅዳር ደኅንነት እንዲያገግም ያስቻለ ስኬታማ ሥራ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በተለይም በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ የህብረተሰቡን የተቀናጀ የተፋሰስ ልማትን ባህል በማጎልበት የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን እያስጠበቀ መሆኑን ተናግረዋል። በዘንድሮ የ2018 ዓ.ም በጀት ዓመትም በ22ሺህ 59 ተፋሰሶች 4 ነጥብ 6 ሚሊየን ሄክታር መሬት ለማልማት በተያዘው ዕቅድ፤ እስካሁን 3 ነጥብ 9 ሚሊየን ሄክታር መሬት በበጋ ተፋሰስ መልማቱን አስታውቀዋል። በአሁኑ ወቅትም በተለያዩ ክልሎች የሥነ-ምኅዳር ሁኔታን ታሳቢ በማድረግ የተፋሰስና የአካባቢ ጥበቃ የልማት ሥራ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። ባለፉት ዓመታት በህብረተሰብ ተሳትፎ የተከናወኑ ሰፋፊ የአፈርና ውሃ ጥበቃ የልማት ሥራዎችም የተራቆተ የመሬት ገፅታ እንዲያገግም በማድረግ ተጨባጭ ውጤት ማምጣቱን አስረድተዋል። የህብረተሰቡ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ ባህል እያደገ መምጣቱም የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ለአብነትም በርካታ ዜጎች በንብ ማነብ፣ እንስሳት መኖ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት መርሃ ግብሮች ተጠቃሚ እየሆኑ እንደሚገኝ አንስተዋል። ይህም የህብረተሰቡን የአካባቢ ጥበቃ ባለቤትነትን በማረጋገጥ ኢትዮጵያ በደን ሀብት የበለጸገች ለምለም ሀገር እንድትሆን እያደረጋት መሆኑን አንስተዋል።  
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል
May 9, 2026 220
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 1/2018(ኢዜአ):- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡ ተገለጸ። በቢሮው የደን ልማት እንክብካቤ ዳይሬክተር አቶ ዘሪሁን ስዩም ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክረምቱ ወቅት ለሚከሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት ተደርጓል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት በክልሉ ተግባራዊ የተደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ- ግብር የደን ሽፋንን በመጨመር፣ የደረቁ ምንጮች እንዲያገግሙ በማድረግ እና የግጦሽ መሬት መጠንን በመጨመር አመርቂ ውጤት ተመዝግቦበታል ነው ያሉት፡፡   በአሁኑ ወቅትም በክልሉ 71 ተራሮችን የማልማት ስራ እየተከናወነ ሲሆን ቡለውጡ አመታት በዘርፉ በተከናወኑ ተግባራት 18 ነጥብ 9 ከመቶ የነበረውን የደን ሽፋን ከ 23 ነጥብ 8 በመቶ በላይ ማድረስ መቻሉንም ተናግረዋል። ይህንን ለማስቀጠልም በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር 180 ሺህ ሔክታር መሬት በተለያዩ ችግኞች ለመሸፈን እየተሰራ ይገኛል ነው ያሉት ። ለዚህም የችግኝ፣ የጉድጓድ እና ሌሎች አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅቶች በበቂ ሁኔታ መደረጉን አመልከተው በአሁኑ ወቅትም የበልግ ወቅት የችግኝ ተከላ ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። የችግኝ ተከላው ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት ትልቅ አበርክቶ እንዳለው አመልክተው ለክረምት ወቅት ተከላ የሚደረገው ዝግጅት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ጠቁመዋል። በዘርፉ የተመዘገበውን ለውጥ ዘላቂነት ለማረጋገጥ ህብረተሰቡ ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ ሊረባረብ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
በዞኑ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ኢኮኖሚያዊ ጠቃሜታ ያላቸው ችግኞች ተዘጋጅተዋል
May 8, 2026 315
ጊምቢ፤ ሚያዝያ 30/2018(ኢዜአ)፦ በምእራብ ወለጋ ዞን ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ኢኮኖሚያዊ ጠቃሜታቸው የጎላ ችግኞች መዘጋጀታቸውን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ፍቅሩ ብርሃኑ እንዳሉት በዞኑ ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተዘጋጅተዋል። ከችግኞቹም መካከል ኢኮኖሚያዊ ጠቃሜታቸው የጎሉ የቡና፣ የአቮካዶ፣ የማንጎ፣ የፓፓያ እና ሌሎች እንደሚገኙበት አስረድተዋል። የችግኝ ተከላው በበጋ ወራት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች ላይ ትኩረት በማድረግ፣ ለእንስሳት መኖ እንዲውልና ለም አፈር በጎርፍ እንዳይወሰድ ለመከላከል ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱ ተገልጿል።   ይህም የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ጉልህ ሚና ይኖረዋል። ችግኞቹን በበጋ ወራት በተከናወኑ የተለያዩ የእርከን ስፍራዎችና የተመረጡ ቦታዎች ለመትከልም እስካሁን ከ117 ሚሊዮን በላይ ጉድ ጓዶች ቁፋሮ መከናወኑን አቶ ፍቅሩ ጠቅሰዋል። ስራውን ለማሳካትም አርሶ አደሩን በማሳተፍ መከናወኑን የጠቀሱት ሀላፊው፤ የግብርና ባለሙያች ድጋፍና ክትትል ስራዎች መጠናከራችውን አንስተዋል። ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች ለመትከል መዘጋጀታቸውን የጠቀሱት ደግሞ የጊምቢ ወረዳ አርሶ አደር ዋኬኔ አምሳሉ ናቸው። ባለፉት ዓመታት የተተከሉ ችግኞችን ጽድቀት መጠን ለማሳደግ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በመሆን በመንከባከብ ከሰውና እንስሳት ንክኪ መጠበቃቸውን ተናግረዋል። ዘንድሮም በመንግስት ከሚለሙት ችግኞች ባለፈ እሳቸው በግላቸው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞችን ማፍላታቸውን ጠቁመዋል። ከዚህ በፊት ለአካባቢ ጥበቃ ትኩረት ባለመስጠታቸው ያጡትን ምርታማነት በሚያካክስ መልኩ በመጪዉ ክረምት የሚተከሉ የተለያዩ የፍራፍሬ ችግኞች በብዛት ማዘጋጀታቸው የገለጹት የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ለሊሳ ኤቢሳ ናቸው። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ በተሰራው ስራ በርካታ ጥቅም በማግኘታቸውም ስራውን ለማስቀጠል ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በጋራ እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
በአማራ ክልል የአረንጓዴ አሻራ ልማት ህብረተሰቡን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ አድርጓል
May 8, 2026 294
ባህር ዳር፤ ሚያዝያ 30/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞች የክልሉን የደን ሽፋን ከማሳደግ ባለፈ ህብረተሰቡን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ማድረጋቸውን የክልሉ አካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ኢኒሼቲቭ የተራቆቱ አካባቢዎችን አረንጓዴ በማልበስና የአካባቢን ሥነ ምህዳር በማስተካከል አርሶ አደሩን ተጠቃሚ እያደረገ ነው።   የአማራ ክልል አካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን ሃላፊ ተስፋሁን አለምነህ ለኢዜአ እንደገለጹት የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር በክልሉ ከተጀመረ ወዲህ በክልሉ የደን ሽፋን ላይ አበረታች ለውጥ ታይቷል። ለዚህም ባለፉት ዓመታት በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ የተተከሉ ችግኞች የክልሉን የደን ሽፋን ቀደም ሲል ከነበረበት 13 ነጥብ 8 በመቶ በአሁኑ ወቅት ወደ 18 ነጥብ 9 በመቶ ማሳደጋቸውን በማሳያነት ጠቅሰዋል።   ልማቱ የተራቆቱ አካባቢዎች በአረንጓዴ እንዲሸፈኑ፣ የአፈር መሸርሸር እንዲቀርና ለምነቱ እንዲጨምር እንዲሁም የከርሰና የገጸ ምድር ውሃ እንዲጨምር አስችሏል ብለዋል። በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ በለሙ አካባቢዎች አርሶ አደሩ የእንስሳት መኖን ጨምሮ የተለያዩ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው ቸግኞችን በመትከል ተጠቃሚ እየሆነ መምጣቱንም አመልክተዋል። በተለይ መርሀ ግብሩ በእንስሳት እርባታ፣ በእንስሳት ማድለብ፣ በወተት ልማትና በንብ ማነብ ሥራ ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ነው ያስታወቁት።   በክልሉ ግብርና ቢሮ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር እስመለዓለም ምህረት በበኩላቸው፣ በዘንድሮ ክረምትም የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች በመትከል አረንጓዴ አሻራን አጠናከሮ ለማስቀጠል ዝግጅት እየተደረገ ነው። እስካሁንም ዘንድሮ ከሚተከለው አጠቃላይ ችግኝ 94 በመቶ የሚሆነው ተፈልቶ ለተከላ መዘጋጀቱን ጠቁመው፣ ለችግኝ ተከላም ከ260 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ተዘጋጅቷል ብለዋል። በአማራ ክልል ባለፈው የክረምት ወቅት ከተተከሉ አጠቃላይ ችግኞች ውስጥ 86 በመቶ የሚሆኑት መጽደቃቸውን በመጀመሪያ ዙር በተካሄደ ቆጠራ መረጋገጡን ከክልሉ ግብርና ቢሮ የተገኘው መረጃ ያሳያል።
በክልሉ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ከ68 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይሸፈናል
May 7, 2026 307
ቦንጋ፤ሚያዝያ 29/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ከ68 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለመሸፈን ታቅዶ የችግኝ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በሀገሪቱ ከፍተኛ የደን ሽፋንና የተፈጥሮ ሀብት ከሚገኝባቸው አካባቢዎች አንዱ ነው። ክልሉ በየዓመቱ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚያከናውናቸው የችግኝ ተከላ ስራዎች፣ ነባር ደኖችን ከመጠበቅ ባለፈ የተራቆቱ መሬቶችን መልሶ ለማልማትና የብዝሃ ህይወትን ለመጠበቅ ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ።   የዘንድሮው የ68 ሺህ ሄክታር መሬት ሽፋን ዕቅድም ይህንን ክልላዊና ሀገራዊ የአየር ንብረት ለውጥ የመቋቋም ስትራቴጂ አካል ያደረገ ነው። የክልሉ ምክትል ርዕሰ-መስተዳድርና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው እንደገለጹት፤ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡ ለዚህም ዘርፈ-ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች የማዘጋጀትና በቴክኖሎጂ የታገዘ የተከላ ቦታ ልየታና መረጃ የማሰባሰብ ስራ እየተከናወነ ነው ብለዋል፡፡ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ከ68 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በደንና በሌሎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ባላቸው ችግኞች ለመሸፈን የሚያስችል የቅድመ ዝግጅት ስራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከአካባቢ ጥበቃ ባለፈ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና የስራ እድል በመፍጠር የዜጎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያሳደገ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ የካፋ ዞን ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ ልማት መምሪያ ምክትል ሀላፊና የተፈጥሮ ሀብት ልማት ዘርፍ ሀላፊ አቶ ታሪኩ ወልደ ሚካኤል በበኩላቸው፣ የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ዝግጅት ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል።   በዞኑ የፍራፍሬ፣ የሻይ፣ የቡናና ሌሎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም በ539 የችግኝ ጣቢያዎች ዘር የማፍሰስና የችግኝ እንክብካቤ ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። የተዘጋጁ ችግኞችም በ36 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የሚተከሉ ሲሆን ቦታ የመለየት እና መረጃ የማደራጀት ስራ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። አርሶ አደሮችም፣ ከዚህ ቀደም የተተከሉ ችግኞች ፀድቀው ውጤት እያሳዩ መሆናቸውን ገልፀው፣ የመርሃግብሩ መጀመር ደንን በአግባቡ ለመጠበቅ ትልቅ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ተናግረዋል።   በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ተከላ መርሃግብር የተለያዩ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች ለመትከል መዘጋጀታቸውን ጠቅሰዋል። የሚተከሉ ችግኞች ፀድቀው አገልግሎት እንዲሰጡ መንከባከብ አስፈላጊ መሆኑን የጠቆሙት አርሶአደሮቹ ፣ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ በርካታ ጥቅም እያገኙ እንደሆነም ገልፀዋል።
በጉጂ ዞን ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እየተተከሉ ነው
May 6, 2026 227
አዶላ ፤ ሚያዝያ 28/2018 (ኢዜአ)፦ በጉጂ ዞን ድርቅና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ መጀመሩን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ወንዶ ሸርቦቴ እንዳሉት፤ በዞኑ ድርቅና የአካባቢ መራቆትን በዘላቂነት ለመቋቋም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ ተጀምሯል፡፡ በዞኑ ለደን፣ ለጥላ ዛፍ፣ ለፍራፍሬ ልማት፣ ለውበትና ለእንስሳት መኖ የሚውሉ ከ98 ሚሊዮን 800 ሺህ በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል፡፡ ከተዘጋጁት ችግኞች ውስጥ እስካሁን 27 ነጥብ 8 ሚሊዮኑ የበልጉን ዝናብ በመጠቀም በ6 ሺህ 726 ሄክታር መሬት ላይ መተከላቸውን ገልጸዋል። በዞኑ እየተተከሉ ያሉት ችግኞች ድርቅና የአካባቢ መራቆትን ከመቋቋም አልፎ በፍራፍሬ ልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያግዙ ናቸው ብለዋል፡፡ ቀደም ብለው የተተከሉ ችግኞች የእንስሳት መኖና የከርሰና ገጸ ምድር ውሀ አቅርቦትን በማሻሻል የህብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደጋቸውን ጠቅሰዋል። በዞኑ አዶላ ወረዳ የዳማ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ሙሉጌታ አሰፋ በበኩላቸው፤ በአካባቢያቸው የሚስተዋለውን የአካባቢ መራቆትና ድርቅ ለመከላከል በሚከናወኑ ተግባራት በንቃት መሳተፋቸውን አስታውሰዋል። ቀደም ብለው የለሙ አካባቢዎችን ከሰውና እንስሳት ንክኪ በመከለል ለመኖ አቅርቦትና ለንብ ማነብ ስራ ላይ በማዋል ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በዘንድሮ የበጋ ወራትም የማሳና የተራራ ላይ እርከን ስራ ላይ ከመሳተፍ ባለፈ በክረምቱ ወቅት የሚተከሉ ችግኞች ማፍላታቸውን ጠቁመዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምድር መራቆትና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል በኩል ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው
May 6, 2026 250
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምድር መራቆትና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል በኩል ተጨባጭ ውጤት እያመጣ መሆኑን የኢትዮጵያ ደን ልማት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የቴክኒክ ኮሚቴ ገለጸ። ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት ላለፉት ተከታታይ ዓመታት ያካሄደችው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር፣ በአካባቢ ጥበቃ በኩል ዓለምአቀፍ ትኩረትን የሳበ ለውጥ ማስመዝገብ ችላለች። እስካሁን ከ48 ቢሊየን በላይ ልዩ ልዩ የችግኝ ዓይነቶችን በመትከል የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት አጠናክራ ቀጥላለች። ይህም የደን ሽፋንን በማሳደግ ረገድ ተጨባጭ ውጤት ያመጣ ሲሆን፤ የአፈር መሸርሸርን በመከላከል እና የውኃ ሀብትን በመጠበቅ ለግብርናው ዘርፍ ዕድገት ዓይነተኛ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ፍጹም አሰፋ (ዶ/ር) በቅርቡ መግለጻቸው ይታወሳል። መርኃ ግብሩ የፍራፍሬ ተከላን በማካተቱ ለምግብ ዋስትና መረጋገጥ እና ለዜጎች ሥርዓተ ምግብ መሻሻል የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተም ይገኛል። የኢትዮጵያ ደን ልማት የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የምድር መራቆትና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል በኩል ተጨባጭ ውጤት እያመጣ ነው፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ምርትና ምርታማነትን በተጨባጭ እንዲጨምር ማድረጉን ጠቅሰው ቀደም ሲል በዓመት በሄክታር ይታጠብ የነበረን 130 ቶን አፈር፣ አሁን ወደ 54 ቶን ዝቅ ማለቱንም ገልጸዋል። በተለይም በበጋ ወቅት በሚከናወኑ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራዎች የአፈር መሸርሸርን መከላከልና የውኃ ሀብቶችን መጠበቅ ተችሏል ነው ያሉት። በጥናት እንደተረጋገጠው የምርት እና ምርታማነት ማደጉን፣ የደን ሽፋን መጨመሩንና የአፈር መሸርሸር መቀነሱን የገለጹት አስተባባሪው፤ አረንጓዴ አካባቢዎችን በማስፋፋት ለኑሮ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም ተናግረዋል። ቀደም ሲል ኢትዮጵያ በዓለም የምግብ ድርጅት እጅግ ውስን ፍራፍሬ ከሚያመርቱ ሀገራት መካከል ትመደብ እንደነበር አስታውሰው፣ በአሁኑ ወቅት ግን ለምግብነትና ለአካባቢ ጥበቃ የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞች ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል። የችግኝ ጣቢያዎችን በማብዛትና ክትትልን በማጠናከር በመርኃ ግብሩ የሚተከሉ የፍራፍሬ ችግኞች መጠንና ጥራት ላይ ተጨባጭ ለውጦች ተመዝግበዋል ብለዋል። በተለይም በ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞች ዝግጅት በልዩ ትኩረት እየተከናወነ እንደሚገኝም ተናግረዋል። አምና 600 ሚየዮን የሚሆኑ የፍራፍሬ ችግኞች መተከላቸውን አውስተው ዘንድሮ ከዚህ በላይ እንደሚሆን አመልክተዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና አካባቢያዊ ፋይዳዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጎለበቱ መምጣታቸውን ጠቁመው፤ የፍራፍሬ ምርቶችን ለውጭ ገበያ፣ ለአምራች ኢንዱስትሪዎችና ለገበያ ማዕከላት ማቅረብ የጀመሩ አርሶ አደሮች መኖራቸውንም ጠቅሰዋል። እነዚህን መልካም ተሞክሮዎች ይበልጥ ለማስፋት የክትትልና ድጋፍ ሥራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) አረጋግጠዋል። በተጨማሪም የፍራፍሬ ምርቶች ማኅበረሰቡ አማራጭ የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኝ በማድረግ ለምግብ ዋስትና መረጋገጥ ጉልህ ሚና እያበረከቱ እንደሚገኙም አብራርተዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋምና የሚቲዎሮሎጂ ዘርፍን ለማዘምን ያከናወነቻቸው ተግባራት አርዓያ የሚሆኑ ናቸው
May 6, 2026 231
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋምና የሚቲዎሮሎጂ ዘርፍን ለማዘመን ያከናወነቻቸው ውጤታማ ስራዎች የአፍሪካን አቅም የሚያሳድጉ መሆናቸውን ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ የዘርፉ ባለሙያዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ከአፍሪካ ሜቲዎሮሎጂ ሶሳይቲ ጋር በመተባበር የመጀመሪያውን ሳይንቲፊክ ኮንፍረንስ በአዲስ አበባ አካሂዷል። በኮንፍረንሱ የተሳተፉ ባለሙያዎች እንደገለጹት፤ የአፍሪካ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም፣ በሚቲዎሮሎጂ እንዲሁም በሃይድሮሎጂ ምልከታዎች ዙሪያ በጋራ መሥራታቸው ወሳኝ ነው። ይህም የተፈጥሮ አደጋዎች ሳይከሰቱ አስቀድሞ ጥንቃቄ ማድረግ የሚያስችሉ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስልቶችን ለማጎልበት እንደሚረዳ አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በዘርፉ ላከናወነቻቸው የቴክኖሎጂና የመሠረተ ልማት ኢንቨስትመንቶች አድናቆታቸውን ገልጸው፤ እነዚህ ኢንቨስትመንቶች ከኢትዮጵያ አልፈው ለአህጉራዊ የኢኮኖሚ ትስስርና የመቋቋም አቅምን ለመገንባት ትልቅ ድርሻ አላቸው ብለዋል፡፡ በተለይም ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ፣ የታዳሽ ኃይልን ከማስፋፋት እና በሌሎች የአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም በሚያስችሉ ተግባራት ዙሪያ ያሳየችው ውጤት የመንግስትን ቁርጠኝነት በተግባር የሚያመላክት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ከዚምባቡዌ የመጡት ፍሪዶ ሙካንጋ በሰጡት አስተያየት፤ በኢትዮጵያ የሚቲዎሮሎጂ ዘርፍን ለማዘመንና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት እጅግ የሚያስደንቁና ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ተነሳሽነትን የሚፈጥሩ ናቸው፡፡ ኢንስቲትዩቱ በመረጃ አያያዝና በከፍተኛ አቅም በሚሰሩ የኮምፒውተር ቴክኖሎጂዎች ላይ ያደረገው ኢንቨስትመንት መንግሥት ለዜጎቹ ሕይወት መታደግ ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ሥነ-ምሕዳርን ከመጠበቅ ባለፈ ለምግብነት የሚውሉ ተክሎች ላይ ትኩረት ማድረጉ፣ ለዜጎች የገቢ ምንጭ እንዲሆንና ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን ማስቻሉን ገልጸዋል። በሃይድሮሎጂ ዘርፍ የሚደረጉ ምልከታዎችና ጥናቶችም ለኃይል ማመንጫ፣ ለመስኖ ልማትና ለግብርናው ክፍለ ኢኮኖሚ ዕድገት የጀርባ አጥንት ለሆኑ ኢንዱስትሪዎች ከፍተኛ እገዛ እያደረጉ መሆኑን መረዳታቸው ጠቅሰዋል፡፡ የታንዛንያው ተወካይ ዶክተር ፍሬድበሪት ኦዱንጋ በበኩላቸው፤ አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን የመቋቋም አቅሟን ለማጎልበት ሀገራት በጋራ መሥራት፣ ግብዓቶችን መጋራት እና የተቀናጁ ስልቶችን መቅረጽ እንዳለባቸው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በውኃ አስተዳደር እና በኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ግድቦች ግንባታ ላይ ያከናወነቻቸው ተግባራት ለአህጉራዊ የአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ጥረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸውም ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ በመሠረተ ልማት ዘርፍ እያከናወነች ያለችው ሰፊ ጥረት ለመላው አፍሪካ የመቋቋም አቅም መጎልበት ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ኬንያዊቷ ማሪያ ሎኪ ቻሬም በበኩላቸው የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትላቸውን ዘርፈ ብዙ ችግሮች በበለጠ ፍጥነትና ውጤታማነት ለመፍታት የአፍሪካ ሀገራት በጋራ መስራት እንደሚገባቸው ጠቅሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ ተሞክሮ ለሌሎች ሀገራት እጅግ ጠቃሚ መሆኑን ጠቅሰው፤ ከኢትዮጵያ ልምድ በመነሳት የአፍሪካ ሀገራት ለአህጉሪቱ ስኬት መሥራት እንዳለባቸውም ገልጸዋል፡፡
በዞኑ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ39 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ችግኝ ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል
May 6, 2026 123
ደሴ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ ዞን በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ39 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ችግኝ ለመትከል ዝግጅት መደረጉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም ቡድን መሪ መገርሳ ተሾመ ለኢዜአ እንደገለጹት ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ በተተከሉ ችግኞች ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል፡፡ የደን ሽፋንን በማሳደግ፣ በተፋሰሶች በእንሰሳት መኖ፣ በንብ ማነብ፣ በፍራፍሬ ልማትና በሌሎችም ለወጣቱ የሥራ እድል በመፍጠር እንዲሁም የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ አበረታች ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል። የተገኘውን ውጤት ለማስቀጠል በዘንድሮ ክረምት በሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርህ ግብር ከ39 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ ችግኝ ለመትከል ዝግጅት መደረጉንና ለዚህም የችግኝ ዝግጅት መከናወኑን ተናግረዋል። የደሴ ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አደም ከድር በሰጡት አስተያየት በየአመቱ ችግኞችን በማፍላት በራሳቸው መሬት በመትከልና የተረፈውን በመሸጥ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በቃሉ ወረዳ ነዋሪ ወጣት አህመድ መሀመድ በበኩሉ በያዝነው በጋ ከ100 ሺህ በላይ የማንጎ፣ ቡና፣ አቡካዶና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች ማዘጋጀቱንና በመጭው ክረምት በመሸጥ ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እየሰራ መሆኑን አመላክቷል። በደቡብ ወሎ ዞን ባለፈው ክረምት ከተተከለው 210 ሚሊየን ችግኝ መካከል ከ75 በመቶ በላይ መጽደቁን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
በጅማ ዞን ለዘንድሮው የአረንጓደ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ዝግጁ ሆነዋል
May 6, 2026 102
ጅማ፤ ሚያዝያ 28/2018(ኢዜአ)፦ በጅማ ዞን ለዘንድሮው የአረንጓደ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ዝግጁ መደረጋቸውን የዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት አስታወቀ። የጅማ ዞን ግብርና ፅህፈት ቤት ሃላፊ ቲጃኒ ተማም፤ ለደን ልማት፣ ለፍራፍሬ፣ ለውበትና የእንስሳት መኖን ጨምሮ ሌሎችንም ባካተተ መልኩ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ለዚህም 91 ሺህ ሄክታር መሬት ለችግኝ መትከያ የተዘጋጀ መሆኑንና ለስኬታማነቱ ከወዲሁ የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ለልማቱ የችግኝ ዝግጅት ከማድረግ በተጓዳኝ ከዚህ ቀደም የተተከሉትን የመንከባከብ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው ዘንደሮም በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ ቀርሳ ወረዳ አርሶ አደር ሙላቱ ደበሌ እና አርሶ አደር ቲጃኒ አባ ጎጀም፤ የሚተከሉ ችግኞች ለምግብ ዋስትና መሰረት እየሆኑ በተግባር እየተጠቀምንባቸው እንገኛለን ብለዋል። ለአካባቢ ጥበቃ፣ ለእንስሳት መኖ እና ምቹ የመኖሪያ አካባቢ ለመፍጠር የሚተከሉ ችግኞች ትልቅ ትርጉም እንዳላቸውም አንስተዋል። በመሆኑም የተተከሉትን ችግኞች በመንከባከብና የተራቆቱ አካባቢዎችን በዛፍ በመሸፈን የበኩላችንን እንወጣለን ነው ያሉት። በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር በንቃት ለመሳተፍ ዝግጁ መሆናቸውንም አርሶ አደሮቹ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከአካባቢ ጥበቃ ባለፈ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የኢኮኖሚ አቅምን ለመገንባት ትልቅ አቅም የሆነ ኢንሼቲቭ ነው።   በተመሳሳይ በጉጂ ዞን ድርቅና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ መጀመሩን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታውቋል። በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ቡድን መሪ ወንዶ ሸርቦቴ እንዳሉት በዞኑ ለደን፣ ለጥላ ዛፍ፣ ለፍራፍሬ ልማት፣ ለውበትና ለእንስሳት መኖ የሚውሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል፡፡ ከተዘጋጁት ችግኞች ውስጥ የበልጉን ዝናብ በመጠቀም በ6 ሺህ 726 ሄክታር መሬት ላይ መተከላቸውን ገልጸዋል። ቀደም ብለው የተተከሉ ችግኞች የእንስሳት መኖና የከርሰና ገጸ ምድር ውሀ አቅርቦትን በማሻሻል የህብረተሰቡን ኢኮሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደጋቸውን ጠቅሰዋል።
የባህር ዳር ከተማን የቱሪስት መስህብነት ይበልጥ የሚያጎሉ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል  
May 5, 2026 180
ባህር ዳር፤ ሚያዝያ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የባህር ዳር ከተማን የቱሪስት መስህብነት የሚያጎሉና የነዋሪዎችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የችግኝ ተከላ ሥራዎችን ለማከናወን ዝግጅት መደረጉን የከተማዋ ግብርና መምሪያ አስታውቋል። በመምሪያው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃ አጠቃቀም ቡድን መሪ አቶ አንዳርጋቸው ይርጋ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የችግኝ ዝግጅቱ በከተማዋ የተገነባውን የኮሪደር ልማትና የከተማዋን ተፈጥሯዊ ውበት ለማድመቅ መሰረት ያደረገ ነው። በተያዘው በጋ የተዘጋጀውን ችግኝ በክረምቱ በከተማዋ በ562 ሄክታር መሬት ላይ ለመትከል እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥም ከ229 ሄክታር በላይ የሚሆነው መሬት ለአንድ ጀንበር የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የተለየ መሆኑን አስገንዝበዋል። በችግኝ ዝግጅቱ እንደ ዱራንታና አሪዮካርፐስ ያሉ ማራኪ የውበት ዛፎች እንዲሁም የቡና፣ የአቮካዶ፣ የማንጎ፣ የፓፓያና ሌሎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ይገኙበታል ብለዋል። በተለይም የውበት ችግኞችን የኮሪደር ልማት በተሰራባቸው አካባቢዎች በመንገድ ዳርና በአረንጓዴ ስፍራዎች በመትከል ባህር ዳርን በቱሪስት መስህብነት የላቀች ለማድረግ እንደሚሰራ አስረድተዋል። በችግኝ ማፍላት ስራውም በ25 የሽርክና ማህበር የተደራጁ 388 ወጣቶችን በማሳተፍ ዘላቂ የገቢ አቅማቸውን እንዲያሳድጉ እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል። ባለፈው ዓመት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተተከሉት ችግኞች ውስጥ 86 ነጥብ አምስት በመቶ የሚሆኑት መጽደቃቸውን በተካሄደ ቆጠራ ማረጋገጥ መቻሉን ጠቁመው ይህም የከተማዋን የደን ሽፋን ከ26 በመቶ በላይ እንዲደርስ አስችሏል ብለዋል። "የንጉሴ፣ ዘይድና ጓደኞቹ" ችግኞች ማፍላት ህብረት ስራ ማህበር ስራ አስኪያጅ ወጣት ንጉሴ ቻሌ እንደገለጸው፤ ካዘጋጁት ከ40 ሺህ በላይ ችግኞች ሽያጭ ከ300 ሺህ ብር በላይ ገቢ ለማግኘት እየሰሩ ነው። የዛሬ 5 ዓመት ሦስት ሆነው በ20 ሺህ ብር ካፒታል በጀመሩት የችግኝ ማፍላት ስራ አሁን ላይ ካፒታላቸውን ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ማድረስ ችለዋል። ከራሳቸው በተጨማሪም ስድስት ቋሚና እስከ 40 የሚደርሱ ጊዜያዊ ሰራተኞችን የስራ እድል ተጠቃሚ ማድረጋቸውን አስገንዝበዋል። "የደረጀ ሰራ ወርቅና ጓደኞቻቸው" ችግኝ ማፍላት ሽርክና ስራ አስኪያጅ አቶ ግዛቸው ሰለሞን በበኩላቸው፤ ከ10 ዓመት በፊት ከጡረታ ጊዜያቸው በኋላ ወጣቶችን በማስተባበር ወደ ስራ እንደገቡ አስታውሰዋል፡፡ በተያዘው በጋም 120ሺህ የተለያዩ ችግኞችን ማፍላታቸውን ጠቁመው ከችግኝ ሽያጩ ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት አተገባበር በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው
May 3, 2026 257
ጅማ ፤ ሚያዝያ 25/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት አተገባበር በምሳሌነት የሚጠቀስና ተጨባጭ መሆኑ ተመላከተ። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂን በመከተል ላይ ትገኛለች። ስትራቴጂው በዋናነት ዘላቂነት ባለው የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም እና በፈጠራ የታገዙ የግብርና እና የኢንዱስትሪ ልምዶችን በማስፋፋት ላይ ያተኩራል። ለአብነትም የአፈር እና ውሃ ጥበቃን ማጠናከር፣ ድርቅ የሚቋቋሙ የሰብል ዝርያዎችን መጠቀም እና ከበካይ ጋዝ ነፃ የሆኑ የኃይል ምንጮችን ማስፋፋት የስትራቴጂው አካላት ናቸው። ይህም ኢትዮጵያ መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለመሰለፍ በምታደርገው ጉዞ ከበካይ ጋዝ ልቀት የጸዳ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ለማስመዝገብ የያዘችው ግብ አካል ነው። ለተግባራዊነቱም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር፣ የታዳሽ ኃይል ልማት፣ ዘመናዊና አረንጓዴ ትራንስፖርት እንዲሁም የግብርና እና ተፋሰስ ልማት ላይ በትኩረት እየሰራች ትገኛለች። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ በኢትዮጵያ የግሎባል ግሪን ግሮዝ ኢንስቲቲዩት (GGGI) ዳይሬክተር እና በኢትዩጵያ የምግብ ስርዓት ሽግግር እና ኒውትሪሽን የአየር ንብረት አስተባባሪ ጋር ቆይታ አድርጓል። የግሎባል ግሪን ግሮዝ ኢንስቲቲዩት በማደግ ላይ ያሉ ሀገራት ሁሉን አቀፍና ለአካባቢ ጥበቃ ትኩረት የሚሰጥ ጠንካራ ኢኮኖሚን እንዲገነቡ እገዛ ያደርጋል።   በኢትዮጵያ የኢንስቲትዩቱ ዳይሬክተር ኦኬቹኩ ዳንኤል ኦግቦናያ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ተቋቁማ ያስመዘገበችው እድገት ቀጠናውን በልማት ለማስተሳሰር ተጨማሪ እቅም እየፈጠረ ነው። የአረንጓዴ የኢኮኖሚ ልማቱም የካርቦን ልቀትን በመቀነስ የስራ እድል እንዲስፋፋና ኢንቨስትመንትን ለመሳብም ተደማሪ አቅም በመፍጠሩ ተሞክሮ የሚወሰድበት መሆኑን ጠቁመዋል። ሀገሪቱ በታዳሽ ኃይል ልማት በውሃ፣ በነፋስና ጸሐይ ላይ የሚደረጉት ግዙፍ ኢንቨስትመንቶችም በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚን ለመገንባት እንደሚያስችላት ተናግረዋል።   በኢትዮጵያ የምግብ ስርዓት ሽግግር እና ኒውትሪሽን የአየር ንብረት አስተባባሪ ከፈለኝ ጌታሁን (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባለፈ የአየር ንብረት ለውጥን ታሳቢ ያደረገ እድገትን መገንባት እንደሚያስችላት ጠቁመዋል። ለዚህም በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጥቅም የሚሰጡ ችግኞች ተከላና የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራዎች ምርታማነት እንዲጨምር ማገዛቸውን አንስተዋል። ኢትዮጵያ የሰሃራ በረሀ መስፋፋትን ተከትሎ በአፍሪካ ቀንድ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ የተደቀነውን ፈተና ለመቋቋም የሚያስችል አቅም አየገነባች መሆኗን አስተባባሪው ገልጸዋል። አትዮጵያ ቀጣናውን በጋራ ልማት ለማስተሳሰር የጀመረችው ተግባርም የሚበረታታ መሆኑንም አክለዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል አስደናቂ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ እየገነባች ነው - አምባሳደር ኦሊቪያ ሌስሊ
May 1, 2026 446
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል አስደናቂ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ እየገነባች መሆኑን በኢትዮጵያ የአየርላንድ አምባሳደር ኦሊቪያ ሌስሊ ገለጹ። የኢትዮጵያ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ በአረንጓዴ አሻራ፣ የውሃ፣ የንፋስና የፀሐይ ታዳሽ ኃይል ምንጮችን በማስፋፋት ዓለም አቀፍ ዕውቅናን ያስገኘ ዕድገት እያመጣ ይገኛል። የበካይ ጋዝ ልቀትን የሚቀንሱ ዘመናዊ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ የትራንስፖርት አማራጮችን ማበረታታትና የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም ዘላቂ ግብርናን የሚያሳልጡ ስትራቴጂክ የልማት አቅጣጫዎች ናቸው። ይህ የተቀናጀ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ የተፈጥሮ ሃብትን በመጠበቅና ዕድገትን በማፋጠን ለቀጣዩ ትውልድ አስተማማኝ መሰረት እየጣለ ይገኛል። በኢትዮጵያ የአየርለንድ አምባሳደር ኦሊቪያ ሌስሊ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አየርላንድ ከኢትዮጵያ ጋር የተለያዩ የትብብር መስኮችን በማጠናከር የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ እየሰራች ነው ብለዋል። ኢትዮጵያም ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ በመገንባት ተምሳሌትና ዓለምአቀፍ ተቀባይነት ያላቸው ስኬቶችን እያስመዘገበች እንደምትገኝ ገልጸዋል። በተለይም በታዳሽ ኃይልና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተመዘገቡ ውጤቶች የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችሉ መሠረቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም አየርላንድ የኢትዮጵያ የልማት አቅጣጫዎችን ለማሳካት በሚደረገው ጥረት ድጋፏን አጠናክራ እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል። የኢትዮ-አየርላንድን የሁለትዮሽ ግንኙነት በሚያጠናክሩ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ባላቸው የልማት መስኮች በአጋርነት እየተሰራ አንደሚገኝም አምባሳደሯ ገልጸዋል። ኢትዮጵያና አየርላንድ ያላቸውን ዲፕሎማሲያዊ ትብብር የበለጠ በማጠናከር በተለያዩ የልማት መስኮች የሚደረጉ ግንኙነቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። አየርላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ሁሉን አቀፍ ትብብር እንደምታጠናክርም አምባሳደሯ አረጋግጠዋል።
ዘንድሮ በሰሜን ሸዋ ዞን በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ከ36 ሺህ ሔክታር በሚልቅ መሬት ላይ ችግኝ ይተከላል
Apr 30, 2026 483
ደብረ ብርሃን፤ ሚያዝያ 22/ 2018 (ኢዜአ)፡- በመጪው ክረምት በሚካሄደው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ከ36 ሺህ ሔክታር በሚልቅ መሬት ላይ ችግኝ እንደሚተከል የሰሜን ሸዋ ዞን ግብርና መምሪያ አስታውቋል። ለመጪው ክረምት አረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር የሚተከሉ 294 ሚሊየን ችግኞች እስካሁን መዘጋጀታቸውን በመምሪያው የተፈጥሮ ሀብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ቡድን መሪ ጌታነህ ተ/ማርያም ገልጸዋል።   በቀሪ ወራትም ፈጥነው የሚደርሱ ችግኞች ላይ በማተኮር የማዘጋጀት ሥራው እንደሚቀጥል ጠቁመዋል። በአጠቃላይም በመጪው ክረምት ከ36 ሺህ 260 ሔክታር በሚልቅ መሬት ላይ ችግኞች እንደሚተከሉ ለኢዜአ ተናግረዋል። ከአሁን በፊት የተተከሉ ችግኞች አርሶ አደሩን በእንስሳት ዕርባታና ማድለብ፣ በንብ ማነብ፣ በመኖ አቅርቦትና በሌሎች የሥራ ዘርፎች በማሰማራት ጥምር ግብርናን ለማስፋፋት ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል ብለዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት የለሙ 1 ሺህ 163 ተፋሰሶች የአፈር ለምነትን በማሻሻል፣ የገጸና ከርሰ ምድር ውኃን በማበልጸግና ለመስኖ ልማት በማዋል የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ማሳደጋቸውንም አክለዋል።
በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ባለማነው የፍራፍሬ ችግኝ ተጠቃሚነታችን አድጓል-አርሶ አደሮች
Apr 29, 2026 346
ሃዋሳ ፤ ሚያዝያ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ያለሙት የፍራፍሬ ችግኝ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንዳሳደገላቸው በሲዳማ ክልል የሸበዲኖ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ በሲዳማ ክልል የሸበዲኖ ወረዳ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያለሙት የፍራፍሬ ችግኞች አድገው ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንዲያረጋግጡ እያስቻሉ ነው፡፡ በወረዳው የፉራ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር መሃመድ ቦጋለ እና አርሶ አደር ሄርቲሞ ሬቢሶ የቡና ችግኝ በማልማት ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡   ችግኞቹን በኩታ ገጠም በመትከል፣ የተፈጥሮ አፈር ማዳበሪያ በማዘጋጀትና ለጥላ የሚሆን እንሰት በመትከል ተገቢውን እንክብካቤ እያደረጉ እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር አቮካዶን ጨምሮ ለምግብነት የሚውሉ ፍራፍሬዎችን በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ በአቮካዶ ልማት የተሳተፉት አርሶ አደር ሙሴ በቴሾ ናቸው፡፡   ላለፉት ስምንት ዓመታት ሁለት ሄክታር በሚጠጋ ማሳቸው ላይ የተሻሻሉ ዝርያ ያላቸው የአቮካዶ ችግኞችን ተክለው በማልማት ምርቱን ለኢንዱስትሪ ፓርኮች እንደሚሸጡም አክለዋል። የወረዳው እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ጽህፈት ቤት የቡና ፍራፍሬና ቅመማ ቅመም ባለሙያ አቶ ደሞዜ ሌዳሞ እንዳሉት በወረዳው በዘንድሮው ዓመት ከ726 ሄክታር በላይ መሬት ላይ የቡና ችግኝ ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል።   በተለይም ቡና በክላስተር በማልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተሰራው ስራ ውጤታማ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ቡናን ጨምሮ ለፍራፍሬና ለምግብት ለሚውሉ ችግኞች ትኩረት መሰጠቱን የገለጹት ደግሞ የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ ናቸው፡፡   በመርሃ ግብሩ ከሚተከሉ ችግኞች መካከል 60 በመቶ የሚሆኑት ለምግብነት የሚውሉ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ በመርሃ ግብሩም አቮካዶ፣ አፕልና ሌሎች ፍራፍሬዎችን ጨምሮ ለእንስሳት መኖም ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል፡፡ በክልሉ ለዘንድሮ ዓመት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከ322 ሚሊዮን በላይ ችግኖች የተዘጋጁ ሲሆን በቡና ችግኝ ተከላ የተጀመረው መርሃ ግብር እስከ መጪው ሃምሌ ወር እንደሚከናወንም አስረድተዋል፡፡
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራና በታዳሽ ኃይል ያስመዘገበችው ስኬት፤ የአየር ንብረት ጥበቃና ዘላቂ ዕድገት የማይነጣጠሉ መሆናቸውን በተግባር ያረጋገጠ ነው
Apr 28, 2026 605
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራና በታዳሽ ኃይል ልማት የአየር ንብረት ለውጥ እና ዘላቂ ዕድገት የማይነጣጠሉ ቋሚ አጀንዳዎች መሆናቸውን በተግባር አሳይታለች ሲሉ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ክላቨር ጋቴቴ ገለጹ፡፡ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከአፍሪካ ሕብረት፣ ከአፍሪካ ልማት ባንክና ሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበር "የአጀንዳ 2030 እና 2063 ግቦችን ለማሳካት የተቀናጀና አሻጋሪ አካሄድ መከተል" በሚል መሪ ሐሳብ ያዘጋጀው 12ኛው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን መካሄድ ጀምሯል።   በየዓመቱ የሚካሄደው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ የአፍሪካ ሕብረትን የአጀንዳ 2030 እና 2063 የዘላቂ የልማት ግቦችን አፈፃፀም ለመገምገም ነው። የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ክላቨር ጋቴቴ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ እና በኢ-ተገማች የዓለም ነባራዊ ሁኔታ ተስፋና ሥጋት እያስተናገደች ነው። በአፍሪካ ቀጣይነት ያለው፣ አካታችና ተወዳዳሪ ኢኮኖሚ ለመገንባት አህጉራዊ ለውጥና ሽግግር ያስፈልጋል ብለዋል። ኢነርጂ፣ መሠረተ ልማት ማስፋፋት፣ ከተማ ከማዘመን ባለፈ በሀገራት መካከል የእሴት ትስስር መፍጠር እንደሚገባ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን መቋቋም የሚያስችል ጠንካራ እርምጃ እየወሰደች መሆኑን በመግለፅ፤ ለአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 ግብ መሳካት ገንቢ ሚና አለው ብለዋል። ኢትዮጵያ የደን ሽፋኗን ለማሳደግ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መትከሏን አስታውሰው፤ በዓለም የደን ልማት ዘርፍ ከፍተኛው ኢኒሼቲቭ መሆኑን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ 95 በመቶ ኃይል ከታዳሽ ኃይል የሚገኝ መሆኑን ገልጸው፤ ይህ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ወሳኝነት አለው ብለዋል። በአረንጓዴ አሻራ፣ በታዳሽ ኃይልና ከተማ ልማት የተመዘገቡ ስኬቶች ከኢትዮጵያ አልፎ ለሌሎች ሀገራት ዘላቂ ዕድገት ገንቢ ሚና እንደሚኖረውም ገልጸዋል። ኢኒሼቲቮቹ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋም የውኃ ደህንነትን ማረጋገጥ፣ መሰረተ ልማትን ማስፋፋት ያስችላሉ ብለዋል። አፍሪካ የአጀንዳ 2030 እና 2063 ዘላቂ ግቦችን ለመፈጸም በምታደርገው ጥረት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል፡፡   የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሉክ ባሃዱር ታፓ፤ በመላው አህጉሪቱ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም በሚያስችሉ ተግባራት፣ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ፣ በዲጂታል ሽግግርና በቀጣናዊ ትስስር ላይ ቁልፍ አመራር መስጠትና ዕውቀትን ማፍሰስ እንደሚገባ አመላክተዋል። ይህ የአህጉሪቱ አቅም ውጤታማ እንዲሆን ሰፊ ኢንቨስትመንት እንደሚፈልግ የገለጹት ፕሬዝዳንቱ፤ በተለይም በጤና፣ በትምህርትና በዲጂታል ልማት ላይ በትኩረት መሥራት እንደሚገባ አሳስበዋል። ዘላቂ ልማት ያለ እኩልነትና ፍትሐዊ የፋይናንስ ሥርዓት ውጤታማ ሊሆን እንደማይችል በማንሳት፤ ቀጣይነት ያለው የአየር ንብረት ፋይናንስ ሥርዓት በመዘርጋት ተጎጂዎችን መድረስ እንደሚገባም ገልጸዋል። ለዚህም አባል ሀገራት የውስጥ ሀብት አሰባሰብን ማሳደግ፣ የግሉን ዘርፍ ማበረታታትና ከአጋር አካላት ጋር በትብብር መሥራት እንዳለባቸው ፕሬዝዳንት ሉክ ባሃዱር ታፓ አሳስበዋል።
በዞኑ በመጪው ክረምት የሚተከሉ 275 ሚሊዮን ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Apr 28, 2026 246
መቱ ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦በኢሉአባቦር ዞን በመጪው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር የሚተከሉ 275 ሚሊዮን ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳሙ ታከለ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በተካሔዱት የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር እና የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ተራቁተው የነበሩ አካባቢዎች ማገገም ችለዋል።   በተጨማሪም ደርቀው የነበሩ ምንጮች መጎልበታቸውን በዘርፉ ከተመዘገቡ ውጤቶች መካከል ተጠቃሽ መሆኑንም ነው የተናገሩት ። ይህንኑ በማጠናከር በመጪው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር 275 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል የቦታ ልየታ ስራ እየተካሔደ መሆኑን ገልጸዋል። በመርሐ -ግብሩ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ላላቸው የችግኝ ዓይነቶች ቅድሚያ ተሰጥቶ እየተሰራ ሲሆን ከዚህም ውስጥ የፍራፍሬ እና ለከብት መኖ የሚውሉ ችግኞችም ተጠቃሽ እንደሆኑ አንስተዋል። የችግኝ ተከላ ስራው 62 ሺ ሔክታር መሬት ላይ ይከናወናል ተብሎ እንደሚጠበቅም ነው የተገለጸው።   አቶ ደረጀ ዓለሙና አቶ ምስጋና ከበደ በኖጳ ወረዳ በችግኝ ማፍላት ስራ ላይ መሰማራት በመቻላቸው ኑሯቸውን ለመደጎም የሚያስችል ገቢ እንዳስገኘላቸው ተናግረዋል። አቶ ጥላሁን አለማየሁና ወንድሙ አሰፋ ደግሞ በግል የተለያዩ ችግኞችን በማዘጋጀትና ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ ለመሆን እየሰሩ መሆኑን ነው የገለጹት። ባለፉት ዓመታት በተመሳሳይ ሁኔታ የፍራፍሬ ችግኞችን በማዘጋጀት እያቀረቡ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስታውሰው ለዘንድሮው ዓመትም የፓፓያ እና የአቮካዶ ችግኞችን እያዘጋጁ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል ላይ ማዕከል ያደረገ ውጤታማ የልማት አቅጣጫ ላይ ናት 
Apr 27, 2026 384
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል ላይ ማዕከል ያደረገ ውጤታማ የልማት አቅጣጫ ላይ ናት ሲሉ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ገለጹ። የአየር ንብረት ኢንቨስትመንት ፈንድስ(CIf) ከኢትዮጵያ መንግሥት እና የአፍሪካ ልማት ባንክ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ዓለም አቀፍ የልምድ ልውውጥ ጉባኤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። በጉባኤው ላይ ምሁራን፣የልማት አጋሮችና ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ጨምሮ አምባሳደሮችና የሀገራት ተወካዮች ተገኝተዋል።   ለሶስት ቀናት በሚቆየው በዚህ ጉባኤ ላይ የተለያዩ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ረገድ ያገኟቸው ውጤቶች ላይ ተሞክሮዎችን አቅርበው የልምድ ልውውጥ እንደሚያደርጉ ይጠበቃል። የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ የዕድገት ራዕይና አቅጣጫ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል ላይ ማዕከል ያደረገ ነው። ለዚህም ታዳሽ ሃይልን ማስፋፋት፣የውሃ አቅርቦት ማሻሻል፣ የተራቆቱ መሬቶች መልሰው እንዲያገግሙ በማድረግ የማህበረሰቡን የመቋቋም አቅም የሚያሳድጉ ውጤታማ ተግባራት መከናወኑን አብራርተዋል። የአዲስ አበባ የኮርደር ልማትና የወንዝ ዳር ልማት ስራዎች ከተማዋን ዘመናዊ ከማድረጋቸውም ባሻገር እድገት ከአካባቢ ጥበቃ ጋር በተናበበ መልኩ እንዴት እንደሚከወን ማሳያ ነው ብለዋል። መንግሥትም ከአየር ንብረት ለውጥ ኢንቨስትመንት ፈንድስ ጋር በጋራ በመሆን በኢትዮጵያ በአማራጭ ሃይል አቅርቦቶች እና ተፈጥሮን መሰረት ያደረጉ መፍትሔዎች ላይ ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑንም አመልክተዋል። የዛሬው የልምድ ልውውጥ ጉባኤ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ዙሪያ ያላትን ተሞክሮ ለማካፈል፤ ከሌሎች ተሳታፊዎችም ለመማር ዝግጁ ናት ሲሉም ገልጸዋል። የአየር ንብረት ኢንቨስትመንት ፈንድስ(CIF) ዋና ስራ አስፈጻሚ ታሪዬ ባድጌሲን በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል በአረንጓዴ አሻራ አርዓያ የሚሆን ተግባር መፈጸሟን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ከዚህ ቀደም ስኬታማ በሆነ መንገድ ማስተናገዷም በዘርፉ ያላትን የላቀ ተሞክሮ ያሳያል ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ፈንድስ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በጋራ የሚያከናውናቸውን ተግባራት አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
በአማራ ክልል ከ22 ሚሊዮን በላይ የቡናና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል
Apr 27, 2026 327
ባህርዳር፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በመጪው ክረምት ለሚካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከ22 ሚሊዮን በላይ የቡናና የሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸው ተገለጸ። ‎በቢሮው የሆርቲካልቸር ባለሙያ አቶ አወቀ ዘላለም ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክልሉ ተስማሚ ስነ-ምህዳርና የአየር ንብረት ያላቸውን አካባቢዎች በመለየት ቡናና ሌሎች ፍራፍሬዎችን በክላስተር የማልማት ስራ እየተካሄደ ነው። ‎በተያዘው በጋ ወቅትም ከፍተኛ ምርት የሚሰጡና በሽታን የሚቋቋሙ ከ22 ነጥብ አራት ሚሊዮን በላይ የቡናና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።   ‎ለተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል ወደ 12 ነጥብ 2 ሚሊዮን የሚጠጋው የቡና ችግኝ ሲሆን ቀሪው ደግሞ የቆላና የደጋ ፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ተናግረዋል። ‎‎ክልሉን በቡናና ፍራፍሬ ልማት ሞዴል ለማድረግም ሽፋኑንና ምርታማነቱን በማሳደግ ላይ በማተኮር የአርሶ አደሩ ዘላቂ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ‎‎‎ለመጪው ክረምት ለተከላ እየተዘጋጀ ያለው ችግኝም ከ32 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ የሚተከል መሆኑን አስረድተዋል። ‎‎በምዕራብ ጎጃም ዞን የጃቢ ጠህናን ወረዳ አርሶ አደር ተፈራ መለሰ ፤ ባለፉት ዓመታት በአንድ ሄክታር መሬት ላይ ቡናን የማልማት ስራ መስራታቸውን ጠቅሰዋል።   በመጪው የክረምት ወቅትም በተጨማሪ ሩብ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝን በኩታ ገጠም ለመትከል አቅደው እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል። ‎‎የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመትከል የተሻለ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን የገለፁት ደግሞ የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ውበት ተስፌ ናቸው። ‎ባለፈው ዓመት የክረምት ወቅት ከተተከሉ ወደ 17 ነጥብ 7 ሚሊዮን የሚጠጋ ቁጥር ያላቸው የቡና፣ የቆላና ደጋ ፍራፍሬ ችግኞች 93 ነጥብ 5 በመቶው መጽደቁን የቢሮው መረጃ ያመለክታል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም