አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል
May 25, 2026 204
አዳማ፤ ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፡- በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት መደረጉን የምሥራቅ ሸዋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር በይፋ ከተጀመረ ጀምሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተተክለዋል። ይህም የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በተጨባጭ በማረጋገጥ ውጤት ማስገኘቱን ጠቁመው፤ የሰብል ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የጎላ አስተዋጽዖ ማበርከቱን ለአብነት ጠቅሰዋል። ለዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብርም ለደን ልማት የሚሆኑ እና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው 269 ነጥብ 5 ሚሊየን ችግኞች በሁሉም ወረዳዎች ችግኝ ጣቢያዎች አማካኝነት መዘጋጀታቸውን አረጋግጠዋል። ዘንድሮ በ45 ሺህ 563 ሔክታር ላይ የችግኝ ተከላ እንደሚካሄድም ነው ያመላከቱት።
የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ለቀጣናው ብልፅግና የላቀ ሚና አለው
May 23, 2026 678
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 15/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር በምሥራቅ አፍሪካ ቀጣና የተረጋጋ ማህበረሰብ ለመፍጠር እንዲሁም ብልፅግናን ለማጎልበት የላቀ ሚና እንዳለው የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የሰላምና ደህንነት ዘርፍ ዳይሬክተር ኮማንደር አበበ ሙሉነህ ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የራሷን የተፈጥሮ ሀብት ከመንከባከብ ባለፈ፣ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ የሚከሰቱ አደጋዎችን በጋራ ለመከላከል የአካባቢውን አገራት አብሮ የመልማት ዕቅድ ይዛ እየሠራች ስለመሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚህም በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ለጎረቤት አገራት በርካታ ችግኞችን ማበርከቷ ይታወቃል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ ኢኒሼቲቭ በኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ የሚከሰቱ የተፈጥሮ መዛባቶችን ለመከላከል፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና አካባቢን ለመታደግ ታስቦ በከፍተኛ ሀገራዊ ቁርጠኝነት እየተተገበረ የሚገኝ ግዙፍ ፕሮጀክት ነው። ይህ ንቅናቄ በአገር ውስጥ ካስገኛቸው ሁለንተናዊ ጥቅሞች ባሻገር፣ ለጎረቤት አገራትና ለጠቅላላው የምስራቅ አፍሪካ ቀጣናዊ ትስስር ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ነው። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ የምታከናውነው የተፈጥሮ ጥበቃ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ለቀጣናው አገሮች የሚተርፍ ከፍተኛ ፋይዳ ያለው ነው፡፡ የኢጋድ ሰላምና ደህንነት ዘርፍ ዳይሬክተር ኮማንደር አበበ ሙሉነህ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤ በቀጣናው እንደ ጎርፍ፣ የበረሃ አንበጣ እና ድርቅ ያሉ ተፈጥሯዊ አደጋዎች የሰዎችን መፈናቀልና ስደት ይፈጥራሉ፡፡ በዚህም ዜጎች ከአካባቢያቸው ችግሩ ወደ ሌለባቸው አካባቢዎችና ድንበሮችን አቋርጠው የሚሰደዱበትን ሁኔታ የሚፈጠር ሲሆን፤ ይህም በቀጣናው ላይ የሚያሳድረው ጫና ቀላል እንዳልሆነ አመልክተዋል። ይህንን ተግዳሮት ለመቋቋም በኢትዮጵያ የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ውጤቶችን እያሳየ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በኢትዮጵያ አሁን ላይ የሚታየው መደበኛ የዝናብ ሁኔታ ስኬት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ተከትሎ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር እየተጠናከረ በሄደ ቁጥር በቀጣናው የተረጋጋ ማህበረሰብ ለመፍጠር፣ ሰላምና ብልፅግናን ለማጎልበት የራሱ የሆነ ከፍተኛ ድርሻ እንዳለው አንስተዋል። ይህንን የኢትዮጵያን መልካም ተሞክሮ በመረዳት እንደ ኬንያ፣ ደቡብ ሱዳን እና ጅቡቲ ያሉ የጎረቤት አገራት ተመሳሳይ አረንጓዴ ልማቶችን እየተከተሉ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ከዋና ዋና ዓላማዎቹ መካከል አንዱ የግብርና እና የአካባቢ ጥበቃ ልማት መሆኑን ያነሱት ዳይሬክተሩ፤ ይህንን የኢትዮጵያን የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር እና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ሀሳብ በጽኑ እንደሚደግፈው ገልጸዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር ባለፉት ዓመታት በከፍተኛ ተነሳሽነት ሲተገበር ቆይቷል። በመርሀግብሩ እስከ 2017 ዓ.ም ድረስ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ጉልህ ድርሻ እየተጫወተ ይገኛል። ይህ ግዙፍ ብሔራዊ የልማት ፕሮጀክት በኅብረተሰቡ ዘንድ ችግኞችን የመትከልና የመንከባከብ በጎ ባህል እንዲዳብርና የአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ እንዲያድግ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል። በተለይም በችግኝ ማፍላት፣ በተከላና ተያያዥ ሥራዎች ላይ ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር በሀገሪቱ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ ይገኛል።
በሚቀጥሉት አሥር ቀናት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎችን ጨምሮ የደቡብ ምዕራብ እና የምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ
May 22, 2026 974
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2018 (ኢዜአ)፦በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎችን ጨምሮ የደቡብ ምዕራብ እና የምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች በርካታ ቦታዎቻቸውን የሚሸፍን ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፤ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ ስፍራዎች ላይ ለዝናብ መፈጠር አመቺ የሆኑ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች አንጻራዊ ጥንካሬ ይኖራቸዋል። ከእርጥበት አዘል የአየር ሁኔታው ጋር ተያይዞም የተሻለ የዝናብ ስርጭት እንደሚኖር ገልጿል። በዚህም በደቡብ፣ በምዕራብ፣ በደቡብ ምዕራብ፣ በደቡብ ምስራቅ፣ በምስራቅ እንዲሁም በስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች የተሻለ የዝናብ መጠንና ስርጭት እንደሚኖር አመልክቷል። በሚቀጥሉት ቀናት ከሚኖሩት የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች በመነሳት፤ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎችን ጨምሮ የደቡብ ምዕራብ እና የምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች ብዙ ቦታዎቻቸውን የሚሸፍን ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ ብሏል። አልፎ አልፎ በውኃ አካላትና በአካባቢ አየር ውስጥ ከሚጠናከሩት የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች በመነሳት፤ በጥቂት የደቡብ፣ የደቡብ ምዕራብ እና የምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች መጠቆማቸውን ገልጿል። ይህም ለግብርና ሥራ በቂ የአፈር ውስጥ እርጥበት እንዲኖር በማድረግ ለሰብሎች፣ ለግጦሽ ሳርና ለመጠጥ ውኃ አቅርቦት አዎንታዊ ተፅዕኖ እንዳለው አስታውቋል። ከተፈጥሮና ሰው ሠራሽ የውኃ ማጠራቀሚያዎችን አቅም ለማሳደግ እንዲሁም ለቋሚ ተክሎችም አዎንታዊ ሚና እንዳለው ገልጿል። በተጨማሪም ለመኸር ሰብሎች የማሳ ዝግጅትና ዘር ለመዝራት፣ ፍሬ በማፍራትና በተለያየ የእድገት ደረጃ ላይ ለሚገኙ የበልግ ሰብሎች የውኃ ፍላጎት መሟላት፣ ለአረንጓዴ ዕፅዋት ልምላሜ፣ ለመጠጥ ውኃና ለግጦሽ ሳር አቅርቦት መሻሻል የጎላ ጠቀሜታ እንዳለው ተጠቁሟል። በተፋሰሶች ላይ ያለውን የእርጥበት ሁኔታ በተመለከተም ባሮ አኮቦ፣ መካከለኛና ታችኛው አባይ፣ በአብዛኛው ኦሞ ጊቤ፣ በላይኛውና መካከለኛው ስምጥ ሸለቆ ከመካከለኛ እስከ ከፍተኛ የገጸ ምድር ውኃ ፍሰት ይኖራቸዋል ብሏል። በላይኛው ገናሌ ዳዋ፣ ኦጋዴን፣ ታችኛው ተከዜ እንዲሁም በላይኛውና መካከለኛው ዋቤ ሸበሌ ደግሞ ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው የገጸ ምድር ውኃ ፍሰት እንደሚያገኙ ይጠበቃል ብሏል። በተጨማሪም ደረቅ የገጸ ምድር ውኃ ፍሰት የሚኖራቸው በአብዛኛው አፋር ደናኪል፣ አይሻ፣ መካከለኛና ታችኛው አዋሽ እንዲሁም በታችኛው ገናሌ ዳዋ መሆኑን የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ ሲል ገልጿል። በሌላ በኩል በበልግ ወቅት የሚኖረው የሙቀት መጠን መጨመርና በሌሊት ደግሞ የሚታየው ወበቅ አንዱ የዚህ ወቅት ክስተት መሆኑን ጠቁሟል። ከሚኖረው ከፍተኛ የፀሐይ ኃይል ጋር ተያይዞም በተለይም በጋምቤላ፣ በአፋር፣ በሶማሌ፣ በቤንሻንጉል-ጉሙዝና በምዕራብ አማራ አካባቢዎች ላይ የቀኑ ከፍተኛ ሙቀት ከ32 እስከ 41 ዲግሪ ሴልሺየስ እንደሚሆን የትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ ብሏል።
በክልሉ ከ261 ሺህ ሔክታር መሬት ላይ ችግኞችን ለመትከል የ ጉድጓድ ቁፋሮ ስራ ተጀምሯል
May 20, 2026 1157
ባህርዳር ፤ግንቦት 12/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ከ261 ሺህ ሔክታር በላይ በሆነ መሬት ላይ ችግኞችን ለመትከል የጉድጓድ ቁፋሮ ስራ መጀመሩን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንደገለፁት የክልሉን የደን ሽፋን ቀድሞ ወደ ነበረበት ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ ነው። በመጭው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ1 ነጥብ 7 ቢሊዮን በላይ የዋንዛ፣ ወይራ ፣ ዝግባ ፣ ፅድ ፣ አኬሺያ ዲከረንስ፣ ባህር ዛፍ፣ የፍራፍሬና ሌሎች ችግኞችን ለመትከል እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የችግኝ ተከላውን በስኬት ለማከናወን እስካሁን 401 ሚሊዮን በላይ ጉድጓዶችን በማስቆፈር ለተከላ ዝግጁ ማድረግ መቻሉን አረጋግጠዋል። በቀጣይም የአረንጓዴ አሻራ ግብን ለማሳካት ተጨማሪ የችግኝ መትከያ ጉድጓዶችን የማስቆፈር ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስረድተዋል። ባጠቃላይ በክረምቱ ለሚካሄደው ችግኝ ተከላ 261 ሺህ 297 ሄክታር መሬት ከወዲሁ ተለይቶ የጉድጓድ መቆፈር ስራው እየተካሄደ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የሰከላ ወረዳ አርሶ አደር መኮነን ልንገር እንደገለጹት ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መጀመሩ ተራቁተው የነበሩ አካባቢዎችን መልሰው በደን እንዲሸፈኑ ለማድረግ አስችሏል። መርሃ ግብሩ ለመኖ ፣ በንብ ማነብና እንስሳት እርባታ እያስገኝ ያለውን ተጠቃሚነት ለማስፋት በመጭው ክረምት በሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በግልና በወል ቦታዎች ችግኝ ለመትከል ጉድጓዶችን እያዘጋጀን ነው ብለዋል። የሚተከሉት ችግኞች አያስገኙ ያለውን ጠቀሜታ በመረዳት በየዓመቱ ችግኞችን እያለማሁ ነው ያሉት ደግሞ በደቡብ ጎንደር ዞን የደራ ወረዳ አርሶ አደር ካሴ መንግስት ናቸው። በመጭው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች ተንከባክበን በማሳደግ ለውጤት ለማብቃት ከወዲሁ ዝግጅት ጀምረናል ነው ያሉት። ባለፈው ክረምት በነቃ የህዝብ ተሳትፎ ከተተከለው ከአንድ ነጥብ አራት ቢሊዮን በላይ ችግኞች ውስጥ 80 በመቶ የሚሆነው መጽደቁን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት በአፍሪካ የሚያጋጥሙ አደጋዎችን ለመከላከል ሀገራት ቅንጅታቸውን ሊያጠናክሩ ይገባል
May 19, 2026 1144
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት በአፍሪካ የሚያጋጥሙ አደጋዎችን ለመከላከል ሀገራት ቅንጅታዊ አሰራራቸውን ሊያጠናክሩ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ከምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የአየር ፀባይ ትንበያ ማዕከል ጋር በመተባበር ለሁለት ተከታታይ ቀናት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየውን 73ኛውን የምስራቅ አፍሪካ የአየር ፀባይ አዝማሚያ ትንተናና ትንበያ ፎረም ተጠናቋል። በፎረሙ የቀጣናው ሀገራት ተወካዮች፣ የዘርፉ ባለሙያዎች፣ የተለያዩ ዓለም አቀፍ አጋር ድርጅት ተወካዮች እና ሌሎች አካላት ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተርና በዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት የአፍሪካ አህጉር ፕሬዚዳንት አቶ ፈጠነ ተሾመ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ባለፉት ሁለት ቀናት በአፍሪካ ቀንድ ዙርያ ያሉ የኢጋድ አባል ሀገራት ያለፈው የበልግና መጪው ክረምት ወቅት የሚጠበቀውን የአየር ጠባይ ትንበያን አስመልክቶ ተወያይተዋል። በዚህም ሁሉም ሀገራት ከራሳቸው ተጨባጭ ሁኔታ በመነሳት የራሳቸውን የሜቲዎሮሎጂ መረጃዎችንና ከአካባቢያቸው አየር ሁኔታ በማገናዘብ ትንበያና ቅድመ ማስጠንቀቅያ የሚሰጡበት ሁኔታ ላይ መነጋገራቸው አንስተዋል። ከአየር ትንበያው በመነሳትም የሚኖረው የአየር ሁኔታ በግብርና፣በውሃ፣በጤና ላይ ሊያደርሰ የሚችለው አሉታዊና አዎንታዊ ተፅእኖ በመገምገም ለቀጣይ ዝግጅት የሚደረግበት መሆኑ ተናግረዋል። እንዲሁም በህይወትና በንብረት ላይ ሊደርስ የሚችለውን የአደጋ ተጋላጭነትን ከመቀነስ አንፃር ጉልህ ድርሻ ያለው በመሆኑ መሰል መድረክ መዘጋጀቱ ጠቀሜታው የላቀ ነው ብለዋል። በአፍሪካ ቀንድ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚያጋጥሙ አደጋዎች በሰውና በንብረት ላይ ከፍተኛ አደጋ እያደረሰ እንደሚገኝ ጠቁመው፤ ይህን ለመከላከል ሀገራት በቅንጅት መስራት አለባቸው ብለዋል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የአየር ንብረት ትንበያ እና የመተግበሪያ ማዕከል(ICPAC) ዋና ዳይሬክተር አብዲ ፊዳር (ዶ/ር) በአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የኢጋድ አባላት ሀገራት መረጃን መሰረት ያደረገ መረጃ በመለዋወጥ በጋራ ሊሰሩ እንደሚገባ አሳሰበዋል።
ለዘንድሮው አረንጓዴ አሻራ እስካሁን ከ8 ነጥብ 6 ቢሊዮን በላይ ችግኝ ተዘጋጅቷል-ግብርና ሚኒስቴር
May 19, 2026 802
አዲስ አበባ፤ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ለዘንድሮ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እስካሁን ከ8 ነጥብ 6 ቢሊዮን በላይ ችግኝ የማዘጋጀት ስራ መከናወኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የአየር ንብረት ተፅዕኖን በመቀነስና የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ ዘርፈ-ብዙ ፋይዳዎችን እያስገኘ ይገኛል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የሀገር በቀል እጽዋቶችንና የተፈጥሮ ሀብቶችን ከመጠበቅ እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥ የሚያሳድረውን አሉታዊ ተፅእኖ ለመከላከልና የዜጎችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ መንግስት የተለያዩ ተግባራትን ከማከናወን አንጻር ግንባር ቀደም ለውጥ አስገኝቷል፡፡ ባለፉት ሰባት ዓመታት በተሰሩት ስራዎች አበረታች ውጤት የተመዘገበ ሲሆን፤ በመርሃ-ግብሩ 48 ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል የሀገሪቱን አረንጓዴ ሽፋን በከፍተኛ ሁኔታ ማሳደግ ተችሏል። የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ ልማት ከተፈጥሮ ኃብት ጥበቃ ባለፈ ዘርፈ-ብዙ ጥቅሞችን የሰነቀ ሲሆን የአየር ንብረት ተጽዕኖን በመቀነስ ለኢትዮጵያ ሀገራዊና ዓለም አቀፋዊ የኢኮኖሚ፣ ማኅበራዊ፣ ዲፕሎማሲያዊ መስኮች ዘርፈ-ብዙ ፋይዳ እያስገኘ ይገኛል፡፡ ዘንድሮ ለሰባተኛ ጊዜ ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ-ግብር በሀገር አቀፍ ደረጃ ሰፊ ዝግጅት በመደረግ ላይ ይገኛል፡፡ የግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፋኖሴ መኮንን ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ ባለፉት ሰባት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ ላይ የተከናወኑ ሥራዎችና የተመዘገቡት አበረታች ውጤቶች ትልቅ ምስክር ናቸው፡፡ የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የሁለተኛው ምዕራፍ ማጠናቀቂያ መሆኑን የገለጹት መሪ ሥራ አስፈጻሚው፤ ቀደም ሲል ከነበሩ የአረንጓዴ አሻራ አፈጻጸሞች የተወሰዱ ተሞክሮዎችን መነሻ በማድረግ የዘንድሮው ዕቅድ በቁጥር ደረጃ ከፍ ያለ መሆኑን አብራርተዋል። በዚህም መሠረት 8 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል ዕቅድ ተይዞ ሰፊ ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውንና አሁን ላይ ለተከላው የሚያስፈልጉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተጠናቀቁ እንደሚገኙ ጠቁመው የስነ-ምህዳር ሁኔታን መሠረት ያደረገ የችግኝ ዝርያዎች መረጣ መከናወኑንም ጠቅሰዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ችግኝ የሚተከሉባቸው ጉድጓዶችን የማዘጋጀት ሥራ በስፋት እየተከናወነ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አሁን ላይ በበርካታ ዜጎች ዘንድ ባህል እየሆነ መምጣቱንና የተሳታፊዎች ቁጥርም ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ መሆኑን ገልጸዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አንድነት በተግባር የሚረጋገጥበት ትልቅ አገራዊ ኩነት በመሆኑ፣ መላው ሕዝብ በኃላፊነት ስሜትና በቀዳሚነት እየተሳተፈበት ይገኛል ብለዋል። ለዘንድሮው የችግኝ ዝግጅት ከተከናወኑ ሥራዎች መካከል 40 በመቶው ሀገር በቀል የደን ዛፎች ላይ ትኩረት ማድረጉን ጠቅሰው፣ 60 በመቶው ደግሞ ለምግብ ዋስትናና ለሌሎች ዘርፈ-ብዙ ጥቅሞች የሚውሉ የፍራፍሬና የኢኮኖሚ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መሆናቸውን አስረድተዋል።
ትውልዱ የአካባቢውን ልምላሜ ጠብቆ በማቆየት የማህበረሰቡን የደን ልማት ባህል ማስቀጠል አለበት-የሀገር ሽማግሌዎች
May 19, 2026 592
ጂንካ፤ ግንቦት 11/2018 (ኢዜአ)፦ትውልዱ የአካባቢውን ልምላሜ ጠብቆ በማቆየት የማህበረሰቡን የደን ልማት ባህል ለማስቀጠል ግንዛቤን እየፈጠሩ መሆኑን የአሪ የሀገር ሽማግሌዎች ገለጹ። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአሪ ማህበረሰብ ደኖችን ጠብቆ የማቆየትና የመንከባከብ ጠንካራ ባህል አለው። በዞኑ ሰሜን አሪ ወረዳ የጎዛ ቀበሌ የሀገር ሽማግሌዎችም ትውልዱ የአካባቢውን ልምላሜ ጠብቆ በማቆየት ለመጪው ትውልድ እንዲያሻግር ግንዛቤ በመፍጠር ደኖችን የመንከባከብ ባህሉን ለማስቀጠል እየሰሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት የሃገር ሽማግሌ አቶ ተክሌ ተረፈ እንደገለፁት፤ በአካባቢው ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲሻገር የቆየ ደኖችን የመንከባከብ እና ጠብቆ የማቆየት ባህል አለ፡፡ ባህሉ ሳይሸራረፍ እንዲቀጥል በደን ተከላና እንክብካቤ ከማሳተፍ ባለፈ የደኖች መኖር ያለውን ጠቀሜታ በተመለከተ ግንዛቤ የመስጠትና የማስተማር ስራ እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በእርሻ ስራ ውጤታማ ለመሆን ደኖችን ጠብቆ ማቆየት ተገቢ መሆኑን ጠቁመው ደን ከሰው ልጅ ህይወት ጋር ጥብቅ ቁርኝት ስላለው እንክብካቤ እንደሚያስፈልገውም አስረድተዋል። ደኖች የተራቆቱባቸው አካባቢዎች በተፈጥሮ አደጋዎች በተደጋጋሚ ሲፈተኑ አስተውለናል ያሉት ደግሞ የሀገር ሽማግሌው ብላታ ቶዳ ናቸው። አዲሱ ትውልድ ይህን በመገንዘብ ደኖችን እንዲንከባከብ፣ በተራቆቱ አካባቢዎች ችግኞችን እንዲተክሉ ግንዛቤ በመፍጠር ትውልዱን የማነፅ ስራ እየሰሩ እንደሚገኙም ገልጸዋል። የአሪ ባህላዊ የዕርቅ ስነ-ስርዓት፣ አፈ-ታሪኮች፣ የመጪው ዘመን ትንበያ እና ሌሎች ባህላዊ ስነ-ስርዓቶች የሚፈፀሙት በደኖች አካባቢ በሚገኝ ትልቅ ዋርካ ስር እንደሆነ የገለፁት ደግሞ አቶ አለማየሁ ታጋ ናቸው። በደኖች አካባቢ የሚፈፀሙ ባህላዊ ስርዓቶች የደኖችን ጥቅም ለአዲሱ ትውልድ ለማስተማር ታስቦ እንደሆነም አመልክተዋል። ደኖች ከሰው ልጅ ህልውና ጋር የተቆራኙ በመሆናቸው አዲሱ ትውልድ ይህን ተገንዝቦ የአካባቢውን ለምላሜ ጠብቆ እንዲያቆይ የማስተማር ስራ እየሰራን ነው ብለዋል። በአሪ ዞን የአካባቢ ጥበቃ እና የአየር ንብረት ለውጥ ጽህፈት ቤት የደን ጥበቃና ቁጥጥር የስራ ሂደት አስተባባሪ አቶ ክንዴ ፍሰሃ በዞኑ ደኖችን ጠብቆ ለትውልድ የማሻገር ጠንካራ ባህል እንዳለ ገልፀዋል። በዞኑ ከ21 ሺህ 700 ሄክታር በላይ መሬት በደን መሸፈኑን ጠቁመው በዚህም 41 ጥብቅ የተፈጥሮ ደኖች እንደሚገኙ ተናግረዋል። በአካባቢው በሚገኘው ደን ውስጥም ለመድኃኒትነት የሚያገለግሉ በርካታ የዕፅዋት ዓይነቶች እንዳሉም አስረድተዋል። በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በዞኑ ከ12 ሚሊዮን በላይ ችግኞች በተራቆቱ አካባቢዎች የሚተከሉ መሆኑን የገለጹ ሲሆን፥ በአሁኑ ወቅትም የአካባቢው የደን ሽፋን እያደገ መምጣቱን አብራርተዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በቁርጠኝነት እየሰራች ነው
May 18, 2026 652
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በቁርጠኝነት እየሰራች መሆኑን የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ ገለጹ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ከምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግስታት (ኢጋድ) የአየር ፀባይ ትንበያ ማዕከል ጋር በመተባበር 73ኛውን የምስራቅ አፍሪካ የአየር ፀባይ አዝማሚያ ትንተናና ትንበያ ፎረም በአዲስ አበባ እያካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በፎረሙ በአፍሪካ ቀንድ ከሰኔ እስከ መስከረም ድረስ የሚኖረው የአየር ንብረት ለውጥ ትንተናና ትንበያ ይቀርባል። በፎረሙ የአገራት ምርጥ ተሞክሮዎች እንደሚቀርቡ ጠቁመው፤ ኢትዮጵያም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብርን ጨምሮ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በወሰደቻቸው እርምጃዎች የተገኙ ውጤቶች የሚቀርቡበት ይሆናል ብለዋል፡፡ በአፍሪካ ቀንድ በሚስተዋለው ተደጋጋሚ ድርቅ፣ ጎርፍና የመሬት መንሸራተት ምክንያት ሰዎች ከመኖሪያ ቀያቸው እንዲፈናቀሉና ለከፋ ጉዳት እንዲዳረጉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይህንን ቀጣናዊ ችግር በዘላቂነት ለመቋቋም ጥራት ያለውና ወቅታዊ የአየር ንብረት መረጃን ማጠናከርና ተደራሽ ማድረግ እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በቁርጠኝነት እየሰራች መሆኑንም አመልክተዋል። በተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (UNDP) የሪዚሊየንስ ሀብ ኦፍ አፍሪካ ዳይሬክተር ዘይኑ ጀማል (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአየር ንብረት ለውጥ ያደጉም ሆነ በማደግ ላይ ያሉ አገራት የጋራ ፈተና ሆኖ መገኘቱን ገልጸዋል። በዚህም ምክንያት በሚከሰቱ የጎርፍ፣ የድርቅና የመሬት መንሸራተት አደጋዎች ዜጎች ለተለያዩ ችግሮች እየተዳረጉ መሆኑን ጠቁመዋል። ለዚህ ችግር ፈጣን ምላሽ መስጠት የወቅቱ አንገብጋቢ ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰው፤ የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም እገዛ ለማድረግ ሁሌም ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ-መንግስታት (ኢጋድ) ምክትል ዋና ጸሐፊ መሐመድ አብዲ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ የአፍሪካ ቀንድ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ተደጋጋሚ አደጋ ከሚደርስባቸው የዓለም አካባቢዎች መካከል አንዱ ነው። ይህንን አደጋ ለመከላከል የአገራት ቅንጅታዊ ስራ እንደሚያስፈልግ ተናግረው፤ ኢጋድም ችግሩን በዘላቂነት ለማቃለል ከአባል አገራትና ከዓለም አቀፍ የልማት ድርጅቶች ጋር ያለውን ትብብር እንደሚያጠናክር ጠቁመዋል። በዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት የቀጣናዊ ትብብር ጽህፈት ቤት ዳይሬክተር ኢሻም አባደር፤ በአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በሚደረገው ርብርብ ድርጅታቸው በፋይናንስና በቴክኒክ ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል፦ በፎረሙ ላይ የቀጣናው አገራት ተወካዮች፣ የዘርፉ ባለሙያዎችና የዓለም አቀፍ አጋር ድርጅቶች ተወካዮች የተገኙ ሲሆን፤ መድረኩ ነገም ቀጥሎ እንደሚውል ተገልጿል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የተፈጥሮን ጉዳት እያከመ ለመሆኑ የሀሮማያ ሐይቅ ህያው ማሳያ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
May 18, 2026 307
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የተፈጥሮን ጉዳት እያከመ ለመሆኑ የሀሮማያ ሐይቅ ህያው ማሳያ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት የሀሮማያ ሐይቅ ዳግም መወለድ አረንጓዴ አሻራ ከሰጠን ፍሬዎች አንዱ ነው ብለዋል። በ1996 ዓ.ም ሙሉ በሙሉ ጠፍቶ የነበረው የሀሮማያ ሐይቅ፣ በአረንጓዴ አሻራ እና በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ጥረት ዛሬ ወደ ቀደመ ውበትና ሥሪቱ ተመልሷል ሲሉም ገልጸዋል። ይህም አረንጓዴ አሻራን ለኢትዮጵያ የውሃ አካላትና ለተፋሰስ ልማት ቁልፍ ኢኒሼቲቭነቱን በተግባር ያረጋገጠ ነው ብለዋል። ይህ ስኬት በመደመር እሳቤ ልማትን ማረጋገጥ ብቻ ሳይሆን፣ የተፈጥሮን ጫና መቋቋም እና መግራት እንደሚቻል ማረጋገጫ ነው ሲሉም አክለዋል። በአካባቢው ስንደርስ ለተደረገልን አቀባበል ምስጋና አቀርባለሁ ነው ያሉት በመልዕክታቸው።
ለቀጣናዊ ዘላቂ ልማት አስተማማኝና ወቅታዊ የአየር ንብረት መረጃ ማጠናከር ይገባል
May 18, 2026 214
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018(ኢዜአ)፦ለቀጣናዊ ዘላቂ ልማት ስኬት አስተማማኝ፣ ጥራት ያለውና ወቅታዊ የአየር ንብረት መረጃን በጋራ ማጠናከርና ተደራሽ ማድረግ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ ተናገሩ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ከምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት( ኢጋድ) የአየር ጠባይ ትንበያ ማዕከል ጋር በመተባበር 73ኛውን የምስራቅ አፍሪካ የአየር ጸባይ አዝማሚያ ትንተናና ትንበያ ፎረም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። በፎረሙ ላይ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ተወካዮች፣ የዘርፉ ባለሙያዎችና የአለም ዓቀፍ ድርጅቶት ተወካዮች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የተለያዩ እርምጃዎችን እየወሰደች ትገኛለች። የምስራቅ አፍሪካ ቀጠና በአየር ንብረት መለዋወጥና ተያያዥ የተፈጥሮ አደጋዎች ተጋላጭ በመሆኑ፣ ይህንን ተፅዕኖ ለመቋቋም አስተማማኝ የመረጃ ልውውጥ ወሳኝ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ተፅዕኖ ለመቋቋም በርካታ አገራዊ ስራዎችን እያከናወነች እንደሚገኝም አብራርተዋል። ከእርምጃዎች መካከል የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርንና የአየር ትንባያ ትንተናዎች የሚቲዎሮሎጂ ትንበያን ዘመናዊ ቴክኖሎጂን ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገኙበት አንስተዋል። በዚህም ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውን ነው የተናገሩት። የአየር ትንበያ ትንተናዎችን ይበልጥ ትክክለኛና ተአማኒ ለማድረግ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግብዓቶችን በጥቅም ላይ ማዋል መቻሉን ዋና ዳይሬክተሩ ጠቅሰዋል። ለቀጠናዊ ዘላቂ ልማት አስተማማኝና ወቅታዊ የአየር ንብረት መረጃ ማጠናከር እንደሚገባ አመላክተዋል። የምስራቅ አፍሪካ ቀጠና በተደጋጋሚ ለድርቅ፣ ለድንገተኛ ጎርፍና ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብ መጋለጡ የጋራ ስጋት መሆኑ በፎረሙ ላይ ተነስቷል። በመሆኑም አገራቱ በየግል ከሚያደርጉት ጥረት ባለፈ፣ በቀጠና ደረጃ ወጥ የሆነና ሳይንሳዊ መረጃን መሰረት ያደረገ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ስራ ላይ ማዋል ይገባቸዋል ብለዋል። የአየር ንብረት መረጃዎችን ማጠናከር አርሶ አደሮች፣ እንስሳት አርቢዎችና የፖሊሲ አውጪዎች አስቀድመው ውሳኔ እንዲያሳልፉና በልማት እቅዶች ላይ ዘላቂነት እንዲያረጋግጡ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ተገልፅዋል። ፎረሙ ነገም ቀጥሎ እንደሚውል ተመላክቷል።
በኦሮሚያ ክልል 2 ነጥብ 7 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ የተፋሰስ ልማት ስራ ተከናውኗል
May 18, 2026 270
አዳማ ፤ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮ የበጋ ወቅት 2 ነጥብ 7 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ የተፋሰስ ልማት ስራ መከናወኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። በቢሮው የደን ልማትና ተፈጥሮ ሀብት እንክብካቤ ዳይሬክተር አቶ ከተማ አብዲሳ ለኢዜአ እንደገለፁት በክልሉ ባለፉት አመታት በተከናወነ የተፋሰስ ልማት ስራ የተራቆቱ አካባቢዎች አገግመዋል። የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ እረገድም አበረታች ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። ተሞክሮውን አጠናክሮ በማስቀጠል በዘንድሮ በጋ ወቅት 2 ነጥብ 7 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ልማቱ መካሄዱን ተናግረዋል። በተፋሰስ ልማት ስራው የጋራና ማሳ ላይ እርከንና ክትር ጨምሮ የተለያዩ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል ። የተፋሰስ ልማት ስራ በተከናወነባቸው ስፍራዎች ላይ በክረምት ወቅት የችግኝ ተከላ ለማካሄድ የጉድጓድ ቁፋሮና ሌሎች ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆኑን አመልክተዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወነው የተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር መሸርሸርና የጎርፍ ተጋላጭነትን በመቀነስ የመሬት ለምነት በመጨመሩ የግብርና ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ ማስቻሉን ጠቅሰዋል። የተራቆቱ አካባቢዎች በማገገማቸው ለሰብል ልማት አመች የሆነ ዝናብና እርጥበት እንዲኖር ማስቻሉን ጠቁመው የገፀ ምድርና የከርሰምድር የውሃ ሀብት በመጨመሩም የመስኖ ልማት በስፋት እንዲካሄድ አመቺ ሁኔታ መፈጠሩን አመልክተዋል። ባገገሙ ተፋሰሶች ላይ የእንስሳት መኖና የፍራፍሬ ልማት እንዲሁም የንብ ማነብ ስራዎች በማካሄድ ለስራ እድል ፈጠራ አይነተኛ ሚና መጫወቱንም ጠቅሰዋል ። የደረቁ ወንዞች፣ ጅረቶችና ሃይቆች ተመልሰው ለሰውና እንስሳት መጠጥ ውሀ ምንጭነት እንዲሁም ለአሳ እርባታና ለሌሎች አገልግሎቶች እንዲውሉ በማስቻል እረገድ ከፍተኛ አስተዋጾ ማድረጉን አስታውቀዋል ።
ቀጣናዊው የአየር ንብረት ትንበያ ፎረም በአዲስ አበባ
May 18, 2026 169
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 10/2018 (ኢዜአ)፡- 73ኛው የታላቁ የአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ትንበያ ፎረም (GHACOF 73) ዛሬ በአዲስ አበባ መካሄድ ይጀመራል። ፎረሙ የሚካሄደው “የአየር ንብረት አገልግሎቶች፤ ለአይበገሬነት እና ዘላቂ ልማት” በሚል መሪ ሀሳብ ነው። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የአየር ንብረት ትንበያ እና የመተግበሪያ ማዕከል(ICPAC) ከልማት አጋሮች ጋር በመሆን ፎረሙን እንዳዘጋጀው ተገልጿል። ስብሰባው ትንበያ ከመስጠት ባለፈ ትንበያዎቹን ወደ ተግባር መቀየር እና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የቅድመ ማስጠንቀቂያና ቅድመ ዝግጅት እርምጃዎችን ማጠናከርን ያለመ ነው። የአየር ንብረት መረጃዎች አርሶ አደሮች፣ የጤና ባለሙያዎችንና የአደጋ ስጋት አመራሮችን በቀጥታ እንዲደግፉ ማድረግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ምክክር እንደሚደረግ ኢጋድ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል። በብሔራዊ የሚቲዎሮሎጂ ተቋማት መካከል ያለውን ትብብር ማጠናከር ሌላኛው የመወያያ አጀንዳ ነው። መድረኩ ለታላቁ የአፍሪካ ቀንድ ግብርና እና የውሃ ሀብት ወሳኝ የሆነውን ከእ.አ.አ ከጁን እስከ ሴፕቴምበር 2026 ያለውን የዝናብ ወቅት ትንበያ ይቀርብበታል። ሚኒስትሮች፣ የምርምር ተቋማት፣ ሰብአዊ ድርጅቶች፣ የሲቪክ ማህበራት እና የግል ባለሀብቶች ይሳተፋሉ። ይህ የተሳታፊዎች ስብጥር ሳይንስን ከፖሊሲ ጋር ለማገናኘት የታለመ ነው። የአየር ንብረት መዛባት የሩቅ ስጋት መሆኑ ቀርቶ በደጃፋችን ላይ ያለ ተጨባጭ አደጋ ነው ያለው ኢጋድ ፎረሙ በታላቁ የአፍሪካ ቀንድ የሚገኙ ማህበረሰቦች በቂ መረጃ እንዲኖራቸውና አስቀድመው ዝግጁ እንዲሆኑ ማስቻል ላይ ትኩረት ያደረገ መሆኑን አመልክቷል። በፎረሙ ማብቂያ የጋራ አቋም መግለጫ ይወጣል ተብሎ ይጠበቃል። የጋራ መግለጫው በቀጣይ ለሚከናወኑ የቅድመ-ማስጠንቀቂያ ተግባራትና ለማህበረሰብ ጥንካሬ ግንባታ ስራዎች እንደ ዋና ግብዓት እንደሚያገለግል ተመላክቷል። ከዋናው መድረክ አስቀድሞ ከባለድርሻ አካላት ጋር የበይነ መረብ ውይይት እና የአየር ንብረት ትንበያ ልማት አውደ ጥናት ተደርጓል። ቀጣናዊ ፎረሙ እስከ ነገ ይቆያል። 72ኛው የታላቁ የአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ትንበያ ፎረም (GHACOF 72) በጥር ወር 2018 ዓ.ም በኬንያ ናይሮቢ መካሄዱ የሚታወስ ነው።
በመዲናዋ ለአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የችግኝ ዝግጅትና አቅርቦት ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል
May 17, 2026 301
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 9/2018 (ኢዜአ)፦በመዲናዋ ዘንድሮ ለሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የችግኝ ዝግጅትና አቅርቦት ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የአዲስ አበባ ከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ገለጸ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው አረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ባለፉት ዓመታት በከፍተኛ ተነሳሽነት ሲተገበር ቆይቷል። በመርሀግብሩ እስከ 2017 ዓ.ም ድረስ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ጉልህ ድርሻ እየተጫወተ ይገኛል። ይህ ግዙፍ ብሔራዊ የልማት ፕሮጀክት በኅብረተሰቡ ዘንድ ችግኞችን የመትከልና የመንከባከብ በጎ ባህል እንዲዳብርና የአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ እንዲያድግ በማድረግ ረገድ ከፍተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል። በተለይም በችግኝ ማፍላት፣ በተከላና ተያያዥ ሥራዎች ላይ ለበርካታ ዜጎች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር በሀገሪቱ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ላይ አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ኢዜአ ያነጋገራቸው በአዲስ አበባ ከተማ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች በችግኝ ዝግጅት ሥራ ላይ የተሰማሩ ዜጎች እንዳሉት፣ ዘርፉ የሥራ ዕድል ከመፍጠሩም በላይ በሀገራዊ የልማት ሥራዎች ላይ የራሳቸውን አዎንታዊ ድርሻ እንዲያበረክቱ አስችሏል። በየካ ክፍለ ከተማ ሱስኒ ችግኝ ጣቢያ በችግኝ ዝግጅት ሥራ ላይ የተሰማሩት ወይዘሮ ሥራ ምናለ፣ ጣቢያው በአካባቢያቸው መኖሩ የሥራ ዕድል እንዳስገኘላቸውና የሥራው ዓላማና ግብም ሂደቱን በደስታ ለማከናወን እንዳነሳሳቸው ገልጸዋል። በተመሳሳይ ወይዘሮ ፅጌ ነጋአብ በበኩለቸው፣ ያዘጋጇቸው ችግኞች በተለያዩ ቦታዎች ተተክለው ከተማዋን ውብ፣ አረንጓዴና ነፋሻማ ሲያደርጉ መመልከት ደስታን የሚሰጥ ነው ብለዋል። ሥነ-ምህዳሩ የተጠበቀ አካባቢን ለመፍጠር በሚደረገው ሀገራዊ ተልዕኮ ውስጥ የራሳቸውን በጎ አሻራ እንዲያኖሩ እያስቻለ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ወይዘሮ ራሔል ዮሐንስ ናቸው። የአዲስ አበባ ከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ የአረንጓዴ ቦታዎች አያያዝ፣ ክትትልና ቁጥጥር ዳይሬክተር አቶ ሲሳይ አጥናፉ፣ የከተማ አስተዳደሩ ማስተር ፕላኑን ተከትሎ የከተማዋን አረንጓዴ ሽፋን 30 በመቶ ለማድረስ ያለሙ ተግባራትን በስፋት እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ግብ ለማሳካትም በቢሮው ሥር በሚገኙ ዘጠኝ የችግኝ ጣቢያዎች እና በዘርፉ በተሰማሩ 285 ማኅበራት አማካኝነት ከፍተኛ የችግኝ ዝግጅትና አቅርቦት ሥራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በተለይም በከተማዋ ዘንድሮ ለተከላ ከሚዘጋጁት ችግኞች መካከል ከ600 ሺህ በላይ የሚሆኑት የፍራፍሬ ችግኞች ናቸው ብለዋል።
የምስራቅ ሐረርጌ ህዝብ የተቀናጀ የአካባቢ ጥበቃና ተፋሰስ ልማት ስኬት በተሞክሮነት የሚቀመር ተምሳሌታዊ ተግባር ነው
May 16, 2026 385
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2018(ኢዜአ)፦ የምስራቅ ሐረርጌ ህዝብ የተቀናጀ የአካባቢ ጥበቃና ተፋሰስ ልማት ስኬት በተሞክሮነት የሚቀመር ተምሳሌታዊ ተግባር መሆኑን የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ እና ከፍተኛ የፌዴራል መንግስት የሥራ ኃላፊዎች በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሐረርጌ ዞን ጉራዋ ወረዳ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና የግብርና ልማት ሥራዎችን ጎብኝተዋል። የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ የተቀናጀ የአካባቢ ጥበቃ ተፋሰስ ልማት የአፈር መሸርሸርን በመከላከል ለግብርና ምርታማነት ትልቅ አቅም እየፈጠረ ነው ብለዋል። በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሐረርጌ ዞን ጉራዋ ወረዳ የተከናወነው አስደናቂ የተቀናጀ የአካባቢ ጥበቃ ተፋሰስ ልማት ስኬትም በምርጥ ተሞክሮነት ሚወሰድ መሆኑን ገልጸዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት በተከናወኑ መጠነ ሰፊ የተቀናጀ የአካባቢ ጥበቃ ተፋሰስ ልማት ሥራም ከ18 ሚሊዮን ሔክታር በላይ መሬት መልማቱን ተናግረዋል። በዚህም የአርሶና አርብቶ አደሩን ማህበረሰብ የልማት ተሳትፎ በማላቅ ከ38 ሚሊዮን በላይ ሔክታር መሬት እንዲያገግም ያስቻለ ውጤት መገኘቱን አንስተዋል። የኢትዮጵያን የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት በትጋት እየሰሩ ለሚገኙ ሁሉ ምስጋና አቅርበዋል። ይህም የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ተቋማት ዕውቅና በማጉላት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ እንድትገነባ እያስቻላት መሆኑን አስረድተዋል። በቀጣይም የተቀናጀ የአካባቢ ጥበቃ ተፋሰስ ልማት ሥራን የበለጠ በማጠናከር ሁለንተናዊ ብልፅግናዋን ያረጋገጠች ኢትዮጵያን ለትውልድ ለማሻገር በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
በኢሉአባቦር ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ የፍራፍሬ ችግኞች ተዘጋጅተዋል
May 16, 2026 301
መቱ፤ ግንቦት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ኢሉአባቦር ዞን በመጪው የክረምት ወቅት የሚተከሉ የተለያዩ ጠቀሜታ ያላቸው የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። በፍራፍሬ ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮች በበኩላቸው በዘርፉ ያላቸው ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። የኢሉአባቦር ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዳሙ ታከለ፤ በዞኑ በልዩ ኢኒሼቲቭ እየተተገበሩ ከሚገኙ ዋና ዋና የግብርና ሥራዎች መካከል የፍራፍሬ ልማት አንዱ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ለዜጎች የምግብ ዋስትና መረጋገጥና ለኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ትልቅ አቅም እየፈጠረ ይገኛል ብለዋል። በዞኑ በልዩ ትኩረት እየተዘጋጁ ከሚገኙት የፍራፍሬ ችግኞች መካከል የአቮካዶ፣ የሙዝ እና የፓፓያ ችግኞች ዋናዎቹ መሆናቸውን አስታውሰዋል። ይህንኑ መልካም ጅምር ይበልጥ ለማጠናከርና ምርታማነትን ለማሳደግ በተደረገው ጥረት፣ በመጪው ክረምት የሚተከሉ ከ45 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ተዘጋጅተዋል ብለዋል። በችግኝ ዝግጅት ሂደቱም ምርታማነታቸው በተረጋገጠ ምርጥ ዝርያዎች ላይ ትኩረት ተደርጎ መሠራቱን ኃላፊው አብራርተዋል። በፍራፍሬ ልማት የተሰማሩ አርሶ አደሮችም ዘርፉ ለምግብ ዋስትናና ለገቢ ምንጫቸው ተጨማሪ አቅም እየሆናቸው መሆኑን ገልጸዋል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል መዘሚል አደም፣ "የምናመርተውን ፍራፍሬ ለአካባቢው ነዋሪዎች በተመጣጣኝ ዋጋ ከመሸጥ ባለፈ፣ ለሌሎች አርሶ አደሮችም የፍራፍሬ ችግኞችን እያቀረብን በዓመት ጥሩ ገቢ እያገኘንበት ነው'' ብለዋል። አርሶ አደር ተካ መሐመድ እና ፈቀደ አረጋ፣ በግብርና ሥራቸው ውስጥ ለፍራፍሬ ልማት ትልቅ ትኩረት መስጠታቸውን ገልጸው፤ ከዚህ ቀደም ከነበረው አሠራር በተሻለ መልኩ የመልማት አቅማቸውን በማስፋት ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። በመጪው ክረምትም በተለይ የአቮካዶ ችግኞችን በስፋት ለመትከል ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል።
በመጪው ክረምት አብዛኞቹ የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ ያገኛሉ
May 15, 2026 410
አዳማ፣ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ በመጪው ክረምት አብዛኞቹ የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ የሚያገኙ መሆኑን የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በመጪው የክረምት ወቅት የሚኖረውን የአየር ጠባይ ትንበያ ይፋ አድርጓል። በትንበያው መሠረት በሀገሪቱ በምዕራብ አጋማሽ መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ የሚጠበቅ ሲሆን፣ በሰሜን ምስራቅና በመካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች ደግሞ መደበኛና ከመደበኛ በታች ዝናብ እንደሚኖር ታውቋል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ ዛሬ በሰጡት መግለጫ፤ የክረምት ወራት ለሰሜን፣ ለምስራቅ፣ ለመካከለኛው፣ ለሰሜን ምዕራብና ለምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ዋና የዝናብ ወቅት መሆኑን አስታውሰዋል። በዝናብ ስርጭቱ ምዕራብ ኦሮሚያ፣ ጋምቤላ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝ እና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ዞኖች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚያገኙ መተንበዩን ገልጸዋል። መደበኛና ከመደበኛ በታች ዝናብ የሚያገኙት ደግሞ ደቡብና ምስራቅ ትግራይ፣ ሰሜንና ደቡብ ወሎ፣ የአፋር ክልል ዞኖች፣ ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች እንዲሁም የመካከለኛውና የደቡብ ኦሮሚያ ዞኖች መሆናቸውን ተናግረዋል። በተመሳሳይ መደበኛና በጥቂት ስፍራዎች ከመደበኛ በታች ዝናብ የሚያገኙት አካባቢዎች ደግሞ የመካከለኛውና የምዕራብ አማራ ዞኖች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የዘንድሮው ክረምት በደቡብ ምዕራብና በምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች ቀድሞ የሚጀምር ሲሆን፣ እስከ ሐምሌ ወር መጀመሪያ ሳምንት ድረስ ሁሉንም የሀገሪቱን አካባቢዎች እንደሚያዳርስ ገልጸዋል። የክረምቱ ዝናብ አወጣጥን በተመለከተም በደቡብና ደቡብ ምዕራብ አካባቢዎች የሚዘገይ ሲሆን፣ በአብዛኞቹ የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎች ላይ ግን ቀድሞ እንደሚወጣ ትንበያው አመልክቷል ብለዋል። በደቡብ ምዕራብና በምዕራብ አካባቢዎች ተደጋጋሚና ከባድ ዝናብ ሊኖር ስለሚችል ቅጽበታዊ ጎርፍ መከሰት፣ በማሳ ላይ ውሃ መተኛትና ለወባ ትንኝ መራባት ምቹ ሁኔታ ሊያጋጥም እንደሚችልም አንስተዋል። በመሆኑም ህብረተሰቡ የውሃ ማፋሰሻ ቦዮችን በማጽዳትና አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ በማድረግ፣ የግብርና ስራዎችንና ማህበራዊ እንቅስቃሴዎችን ከትንበያው ጋር በማጣጣም እንዲያከናውን ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል።
የአየር ጠባይ ስጋቶችን ለመቋቋም የሚቲዎሮሎጂ መረጃን መሠረት ያደረገ ቅድመ ዝግጅት ያስፈልጋል
May 15, 2026 339
አዳማ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦ የአየር ጠባይ ስጋቶችን ለመቋቋም በሚቲዎሮሎጂ የትንበያ መረጃ መሠረት ዝግጅት ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን የውኃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የ2018 የበልግ ወቅት የአየር ጠባይ ትንበያ ግምገማና የመጪው የክረምት ወቅት የአየር ጠባይ አዝማሚያ ትንበያ ይፋ ለማድረግ ያዘጋጀው የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ በአዳማ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ ላይ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚና የማህበረሰቡ ኑሮ ከወቅታዊ የአየር ጠባይ ሁኔታ ጋር በቀጥታ የተቆራኘ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም እንደ በልግ እና ክረምት ያሉ ወቅቶች ለግብርና ምርታማነት፣ ለውኃ ሀብትና ለኢነርጂ አቅርቦት ያላቸው ፋይዳ የጎላ መሆኑን ጠቁመዋል። በዚህ ረገድ ኢንስቲትዩቱ ለማህበራዊ፣ ኢኮኖሚ እና ለሕብረተሰቡ የሚውሉ የሚቲዎሮሎጂ ትንበያና የቅድሚያ ማስጠንቀቂያ አገልግሎቶችን በወቅቱና በብቃት የማሰራጨት ተግባር እያከናወነ ይገኛል ብለዋል። የዛሬው መድረክ የመጪውን የክረምት ወቅት ትንበያ ይፋ የሚደረግበት በመሆኑ፤ ለአርሶና አርብቶ አደሩ፣ ለውኃ ሀብት አስተዳደር ተቋማት፣ ለአደጋ ስጋት ሥራ አመራርና ለሌሎችም የልማት ዘርፎች ቀድሞ ለመዘጋጀት እጅግ ወሳኝ ነው ብለዋል። በመሆኑም የአየር ጠባይ ስጋቶችን ለመቋቋም የሚቲዎሮሎጂ መረጃን መሠረት ያደረገ ቅድመ ዝግጅት አስፈላጊ መሆኑን አስገንዘበዋል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ በበኩላቸው፤ ተቋሙ የአየር ጠባይ ለውጥን ለመቋቋም፣ የአደጋ ተጋላጭነትን ለመቀነስና አስቀድሞ በመተንበይ የደንበኞችንና የባለድርሻ አካላትን ፍላጎት ለማርካት በትጋት እየሠራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ለዚህም ከዋናው መሥሪያ ቤት ከሚሰጠው አገልግሎት በተጨማሪ 11 የክልል የሚቲዎሮሎጂ ማዕከላትን በማደራጀት መረጃን በቅርበት ተደራሽ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። ኢንስቲትዩቱ ዕለታዊ የአየር ሁኔታ ትንበያ ከመስጠት ባለፈ፤ የረጅም ጊዜ የአየር ጠባይ ትንበያን በመተንተንና በመገምገም ለተለያዩ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች የቅድመ ማስጠንቀቂያ አገልግሎት በወቅቱና በብቃት ለማሰራጨት እየሠራ መሆኑን አመልክተዋል። ይህም መረጃ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ በተለይም ለግብርና እና ለውኃ ዘርፍ የሚሰጠው ፋይዳ ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል።
በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 700 ሺህ ሔክታር መሬት በተለያዩ ችግኞች ለመሸፈን ዝግጅት ተደርጓል
May 15, 2026 295
ገንዳውኃ፤ ግንቦት 7/2018 (ኢዜአ)፦በምዕራብ ጎንደር ዞን በመጪው ክረምት በሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በ700 ሺህ ሔክታር መሬት ላይ የተለያዩ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት መደረጉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታውቋል፡፡ በመምሪያው የደን ባለሙያ አቶ ጋሻው ታያቸው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በመጪው ክረምት ወቅት በሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ሀገር በቀል የሆኑ የደን ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ ነው። ለዚህም ከአንድ ነጥብ ሶስት ሚሊዮን በላይ ችግኞች የተዘጋጁ ሲሆን የችግኞቹ ዝርያ በአካባቢው ያለውን ሞቃታማ የአየር ፀባይና ስነ- ምህዳር የተላመዱ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። ችግኞቹን ለመትከልም እስከ አሁን ከ80 ሺህ በላይ ጉድጓዶች ተቆፍረው የተዘጋጁ ሲሆን፤ ሽመል ፣ አካሻ ሰኔጋል ፣ ኒም ፣ ዋንዛና ሌሎች ዝርያዎችም እንደሚገኙበት ነው ያስረዱት። በዞኑ የመተማ ወረዳ ኩመር አፍጥጥ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር መኮንን ውቤ እንዳሉት፣ በአካባቢያቸው የነበሩ ግዙፍ ዛፎች በመመንጠራቸው የዝናብ መዛባትና የሙቀት መጨመር ሲያጋጥም ቆይቷል። ይህንን ችግር በመሰረታዊነት ለመቅረፍም ሀገር በቀል ችግኞችን በማፍላት ነባር ደኖችን ለመተካት እየተሰራ ያለው ስራ የሚያስደስት ነው ሲሉ ገልፀዋል። ችግኞቹ ድርቅን የመቋቋም አቅማቸው ከፍተኛ በመሆኑ በወቅቱ በመትከልና በመንከባከብ የጽድቀት መጠኑን ለመጨመር በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ ተናግረዋል። አርሶ አደር ስመኘው አዱኛ በበኩላቸው፤ የተዘጋጁት ሀገር በቀል ችግኞች ለአፈር ለምነትና ለከብቶቻቸው መኖ ጠቃሚ መሆናቸውን አብራርተዋል። የግብርና ባለሙያዎች የሚሰጡንን ምክር በመከተል በችግኝ ተከላው ላይ በግንባር ቀደምነት ለመሳተፍ ተዘጋጅተናል ሲሉም አረጋግጠዋል።
በክልሉ ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኞችን በሳይንሳዊ መንገድ በመትከል የጽድቀት መጠናቸውን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
May 15, 2026 209
አዳማ፤ ግንቦት 7/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኞችን በሳይንሳዊ መንገድ በመትከል የጽድቀት መጠናቸውን ለማሳደግ በቂ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በክልሉ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ ችግኞች መዘጋጀታቸውም ተገልጿል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉና ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኞችን የጽድቀት መጠን ለማሳደግ፤ የችግኝ መትከያ ጉድጓዶችን በተገቢው ሁኔታ በማዘጋጀት በቂ አየርና የአፈር እርጥበት እንዲያገኙ ማድረግ ተገቢ መሆኑ ተመላክቷል። በቦታ መረጣ ወቅት የውኃ እጥረት እንዳይኖር የውኃ ማጠራቀሚያ ገንዳዎችን መሥራትና ችግኞቹ ለአካባቢው የአየር ንብረት ተስማሚ መሆናቸውን ማረጋገጥ የትኩረቱ አካል ነው። በተጨማሪም የችግኞች በሽታን የመቋቋም አቅም መኖር፣ ከተተከሉ በኋላ ከእንስሳት ንክኪ መከላከል እንዲሁም ቀጣይነት ያለው የክትትል ሥራ ማከናወን ለጽድቀታቸው ድርሻው የጎላ መሆኑ ተጠቁሟል። የኦሮሚያ ግብርና ቢሮ የደን ልማትና ተፈጥሮ ሀብት እንክብካቤ ዳይሬክተር ከተማ አብዲሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በለውጡ ዓመታት በክልሉ የተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተግባራት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በዘላቂነት በመቋቋም ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ እያገዙ ነው። መርሃ ግብሩን ከአካባቢ ጥበቃና ደን ልማት ጋር በማስተሳሰር ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግና የአካባቢውን ሥነ-ምህዳር ለመጠበቅ በተደረገው ጥረት አበረታች ውጤት መገኘቱንም ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል። ይህንኑ ተግባር ለማስቀጠል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተለያዩ ጥቅሞች የሚውሉ ችግኞች መዘጋጀታቸውንና የተከላ ሂደቱ በሳይንሳዊ መንገድ እንዲከናወን ለአርሶ አደሩ ሥልጠና መሰጠቱን ጠቁመዋል። በመጪው ክረምት ለተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል ለደን፣ ለውበትና ለምግብነት የሚውሉ ፍራፍሬዎች እንደሚገኙበት ጠቁመው፤ ለዚህም የመሬት ልየታ፣ ካርታ የማዘጋጀትና የጉድጓድ ቁፋሮ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል።
የዱር እንስሳትን እና መኖሪያ አካባቢያቸውን የመጠበቅና የማልማት ሥራ ይጠናከራል
May 14, 2026 542
ሮቤ፤ ግንቦት 6/2018(ኢዜአ)፦ የዱር እንስሳትና መኖሪያ አካባቢያቸውን በመጠበቅና በማልማት ለቱሪዝም መስህብነት የማዋል ሥራው እንደሚጠናከር የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ገለጸ። የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ጥበቃን ይበልጥ ለማጠናከር ታሳቢ ያደረገ ሁለተኛው ዙር የዱር ሕይወት ጠባቂዎች (ሬንጀሮች) ምረቃ ተካሂዷል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ ዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ኩመራ ዋቅጅራ እንደገለጹት፤ የዱር እንስሳትና መኖሪያ አካባቢያቸውን በመጠበቅና በማልማት ለቱሪዝም መስህብና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የማዋል ሥራ በትኩረት እየተከናወነ ነው። ባለስልጣኑ የሀገሪቱን የተፈጥሮ ጸጋዎች ለላቀ ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ለማዋል፣ የዱር እንስሳትንና መኖሪያ አካባቢያቸውን የመጠበቅና የማልማት ሥራን በልዩ ትኩረት እያከናወነ መሆኑን አስታውሰው፣ ይህም የቱሪዝም መስህብነትን በማሳደግ ረገድ ጉልህ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። ባለሥልጣኑ ባለፉት ስልሳ ዓመታት የዱር እንስሳትና መኖሪያ አካባቢያቸው ተጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፉ የተለያዩ የጥበቃና የልማት ሥራዎችን ሲያከናውን እንደቆየና ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አንስተዋል። በፓርኮች ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ ተፅዕኖዎችን በመከላከል የጥበቃና የልማት ሥራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር በተከናወኑ ሥራዎች አበረታች ለውጦች እየተመዘገቡ መምጣታቸውንም አመልክተዋል። የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክን ለማልማትና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታውን ይበልጥ ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ የኢኮ-ቱሪዝምና ሌሎች የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች የጥረቱ ማሳያዎች እንደሆኑም አንስተዋል። ዋና ዳይሬክተሩ እንዳሉት፣ የዱር ሕይወት ጠባቂዎች (ሬንጀሮች) መመረቅ በዘርፉ የሚታዩ ህገወጥ ተግባሮችን ለመከላከልና የተፈጥሮ ኃብት ጥበቃ ሥራውን ይበልጥ ለማጠናከር የሚያስችል ነው። የዱር እንስሳትና የመኖሪያ አካባቢያቸውን ከጥፋት ለመታደግ ከዘላቂ የቱሪዝም ልማት ጋር በማጣመር ለኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዲውሉ ማድረግ ይገባል ሲሉም ዳይሬክተሩ አመልክተዋል። የባሌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ አብርሃም ኃይሌ በበኩላቸው እንዳሉት፤ ብሔራዊ ፓርኩን ከተለያዩ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች ለመከላከል ከፓርኩ አስተዳዳርና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ ነው። በዚህም ከዚህ በፊት ይስተዋሉ የነበሩ ተግዳሮቶች እየቀነሱ፤ የጥበቃና የልማት ተግባራትም እየተሻሻሉ መጥተዋል ብለዋል። የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ኃላፊ ሻሚል ከድር በበኩላቸው፤ በፓርኩ ለሦስት ወራት በጥበቃና ሌሎች መሰል ሥራዎች ላይ ስልጠና የወሰዱ 44 ሬንጀሮች መመረቃቸውን ገልጸዋል። ሬንጀሮቹ በጥበቃ ሳይንስ፣ በስና ምግባር፣ በአካል ብቃትና ሌሎች ክህሎቶችን ማግኘታቸውን ተናግረዋል። ተመራቂ ሬንጀሮች በበኩላቸው በሰጡት አስተያየት፤ የወሰዱት በተግባር የተደገፈ ዘመናዊ ሥልጠና በእውቀት ላይ የተመሰረተ የጥበቃ ሥራን ለማከናወን እንደሚያግዛቸው ተናግረዋል። ለሥልጠናው መሳካት አስተዋጽኦ ለነበራቸው አካላት እውቅናና የምስክር ወረቀት የተሰጠ ሲሆን የተለያዩ ባለድርሻ አካላትም ፓርኩን ጎብኝተዋል። በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባሕል ድርጅት (ዩኔስኮ) የዓለም ቅርስ ሆኖ የተመዘገበው የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ የደጋ አጋዘን፣ ቀይ ቀበሮና ሌሎች በርካታ የዱር እንስሳትና ዕጽዋት መገኛ ነው።