አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ሀገራት ለዓለም አቀፍ ቃል ኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል
Mar 5, 2026 55
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018 (ኢዜአ)፡-የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አስከፊ ተፅዕኖ ለመቀነስ ሀገራት ለዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃል ኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ገለጸ። የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት ይጠበቅባቸዋል ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ተፈፃሚነት ያላት ቁርጠኝነት ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ እንዳስቻላት በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአየር ንብረት ተቋማዊ ልማት አማካሪ መንሱር ደሴ ገልጸዋል። ከየካቲት 23/2018 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ አራት ቀናት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና የአውደ ጥናት የምክክር መድረክ ተጠናቋል። በአውደ ጥናቱ ማጠናቀቂያ ላይ የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ፤ የአካባቢና የሥነ-ምኅዳር ደኅነንት ለማስጠበቅ ትብብርን ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል። አውደ ጥናቱም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ተግባራዊ የተደረጉ መርሃ ግብሮችና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ስኬታማ የልምድ ልውውጥና ግብዓት እንደተገኘበት ገልጸዋል። በፖሊሲዎችና የትኩረት መስኮች የተደረገው ውይይትም የዕውቀት ሽግግር የተደረገበት መሆኑን ተናግረዋል። ዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የመንግሥታቱን ድርጅት የአየር ንብረት ስምምነት መነሻ በማድረግ ለተለያዩ ሀገራት የገንዘብ ድጋፍ እያቀረበ እንደሚገኝ አንስተዋል። ሀገራትም የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አስከፊ ተፅዕኖ ለመቀነስ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚያደርጉትን ጥረት እንደሚያግዝ አረጋግጠዋል። በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአየር ንብረት ተቋማዊ ልማት አማካሪ መንሱር ደሴ በበኩላቸው፤ በአውደ ጥናቱ ከ14 የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ 150 ሙያተኞች መሳተፋቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ትግበራ ያላት ቁርጠኝነት በልማት አቅጣጫዎቿ ላይ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን አስረድተዋል። በአውደ ጥናቱም ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በተደረገ ድጋፍ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች በተሞክሮነት መቅረባቸውን ተናግረዋል። ከሀምሌ ወር ጀምሮ ለአራት ዓመታት የሚተገበረው የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም መርሃ ግብርም ከኢትዮጵያ የልማት አቅጣጫዎች ጋር ተጣጥመው እንደሚተገበሩ አንስተዋል።
በምስራቅ ሸዋ ዞን የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት ያደረጉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Mar 4, 2026 169
አዳማ ፤ የካቲት 25/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት ያደረጉና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማፍላት ስራ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ ነው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ሃገራዊ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ሐምሌ 2011 ዓ.ም መጀመሩ ይታወቃል። በምስራቅ ሸዋ ዞን ግብርና የጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በዞኑ 11 ወረዳዎች ባሉ የችግኝ ማፊያ ጣቢያዎች ለመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ ተጀምሯል። ችግኝ ጣቢያዎቹ ለአረንጓዴ አሻራ ዘመቻው የተለያየ ዝርያ ያላቸው ችግኞችን አፍልቶ በማቅረብ ረገድ እያበረከቱ ያለው አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን አስታውሰዋል። ዘንድሮም ለማዘጋጀት ከታቀደው ከ284 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ውስጥም 241 ነጥብ 4 ሚሊዮን ችግኞችን የማፍላት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። ቀሪ ችግኞችን የማፍላት ሥራም እስከ መጪው ግንቦት ወር ድረስ ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በችግኝ ዝግጅቱም በአብዛኛው የአየር ንብረት መዛባትን ለመከላከል ለሚያገለግሉ የደን እና ጥምር ደን ዝርያዎች ትኩረት የተሰጠ መሆኑን አስረድተዋል። በተጨማሪም ለአርሶ አደሩ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን የሚያስገኙና እና ለምግብነት የሚውሉ 26 ነጥብ 7 ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኞችን ያካተተ የዘር ዝግጅት መደረጉንም ተናግረዋል። የዘንድሮ ዓመት የችግኝ ተከላ የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት በማድረግ የሚከናወን መሆኑን ጠቁመው በዞኑ ባለፉት ዓመታት ከተተከሉ ችግኞች ከ85 በመቶ በላይ መጽደቃቸውን አስታውቀዋል። በአሁኑ ወቅትም የተተከሉ ችግኞችን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ የመጠበቅና የመንከባከብ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ነው ያረጋገጡት። በዘንድሮው ዓመት በዘርፉ የተቀመጠውን እቅድ ለማሳካትም የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ተቆፍረው መዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል።
የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት ይጠበቅባቸዋል
Mar 3, 2026 171
አዲስ አበባ፤ የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፦የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት እንደሚጠበቅባቸው የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) ገለጸ። "በምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ የሚቋቋም ግብርናን ማስፋፋት" በሚል መሪ ሃሳብ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ቀጣናዊ የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። በኢጋድ፣ የዓለም ባንክ የአፍሪካ ቢሮ፣ የሥርዓተ ምግብ ፕሮግራም ለምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ፣ የደቡባዊ አፍሪካ የግብርና ምርምርና ልማት ማስተባበሪያ ትብብር በተዘጋጀው መድረክም የግብርና ማሻሻያ ምክረ ሀሳቦችን እንደሚያፈልቅ ይጠበቃል። የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) ተወካይ ዳህር ኤልሚ፤ በአየር ንብረትና በሥነ-ምኅዳር ደኅንነት የሚከሰት ለውጥ የግብርና ምርታማነት ላይ ጫና እያሳደረ ነው ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለው የአፈር መራቆት፣ ድርቅ፣ ጎርፍ፣ ዝናብ እጥረትና በርሃማነት የምስራቅ አፍሪካ የግብርና ምርታማነትና የምግብ ፍጆታ ላይ አሉታዊ ጫና እንደሚያሳድሩ ገልጸዋል። በዚህም የቀጣናው ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት ለመገንባት የቴክኖሎጂ፣ የግብዓትና የመረጃ ትንተና አቅም መገንባት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣንም የቀጣናውን ሀገራት የግብርና ምርታማነት የሚያሻሽል የአየር ሁኔታ የመረጃ ትንተና ተደራሽ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት የተፈጥሮ ሃብትና የአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ፕሮግራም ዳይሬክተር አወቀ ሙሉዓለም በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ሥርዓት ውጤት እያስመዘገበ ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችም የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ በማድረግ የአርሶና አርብቶ አደሩን የግብርና ምርታማነት እያሳደገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዓለም ባንክ ከፍተኛ የግብርና ባለሙያ ቲም ሮበርትሰን፤ የግብርና ምርታማነት የሚያዘምኑ የፋይናንስና የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በማስፋት የቀጣናው ሀገራት አርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል። በኢትዮጵያ የኒውዝላንድ አምባሳደር የኢጋድና የአፍሪካ ሕብረት ቋሚ ተወካይ አምባሳደር ኦሊቪያ ኦዌን በበኩላቸው፤ የግብርና ምርታማነትን ማረጋገጥ ለአፍሪካ ዕድገትና ብልጽግና ወሳኝ ነው ብለዋል። የቀጣናውንና አፍሪካን የግብርና ሥርዓት ለማዘመን በሚደረገው ጥረትም የኒውዝላንድ መንግስትና የልማት አጋሮች የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በፎረሙ ላይ የኢጋድ አባል ሀገራት ተወካዮች፣ ፖለሲ አውጪዎች፣ የልማት አጋሮች፣ የግሉ ዘርፍ ተወካዮችና ተመራማሪዎች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ስርጭትና መጠን ይጠናከራል
Mar 3, 2026 105
አዲስ አበባ፤ የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፦በቀጣዮቹ አስር ቀናት በሀገሪቱ የበልግ ሰብል አብቃይ አካባቢዎች የዝናብ መጠንና ስርጭት በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋና እየተጠናከረ እንደሚሄድ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ አራተኛውን የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስራ ሊያስጀምር ነው በኢንስቲትዩቱ የሚቲዎሮሎጂ ትንበያ፣ምክር አገልግሎት እና ምርምር ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አሳምነው ተሾመ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለዝናብ መፈጠር ምቹ የሆኑ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች ይበልጥ እየተጠናከሩ መሆናቸውን የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ። የዝናብ ስርጭቱ የሚሸፍናቸው ደቡብና ደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያ (ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው የሆኑ አካባቢዎች)፣ የስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎች፣ የመካከለኛውና የደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች ምስራቅና ሰሜን ምስራቅ አካባቢዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። በእነዚህ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ የሚጠበቅ ሲሆን፣ በአብዛኛው ስፍራዎች የዝናብ መጠኑ መደበኛና ከመደበኛ በላይ እንደሚሆን ገልጸው፤አልፎ አልፎም ከባድ ዝናብ ሊኖር እንደሚችል ተናግረዋል። የዝናቡ መሻሻል በተለይም ለበልግ አብቃይ አርሶ አደሮች ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል። በበልግ እየጣለ ያለው ዝናብ የማሳ ዝግጅትና ዘር፡ የአፈር እርጥበትን በማሻሻል አርሶ አደሩ የተለያዩ ሰብሎችን መዝራት እንዲችል ምቹ ሁኔታን በመፍጠር አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። ለቋሚ ተክሎች፡ ቀደም ብለው ለተዘሩ የበልግ ሰብሎችና በአካባቢው ለሚገኙ ቋሚ ተክሎች ዕድገት ያለውን አስተዋጽኦም ገልጸዋል። ለውሃ አጠር አካባቢዎችም አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ የሚጥለውን የዝናብ ውሃ በማሰባሰብና በማከማቸት ለቀጣይ እንዲጠቀም ምክረ ሀሳብ አቅርበዋል። በበልግ የሚጥለው ዝናብ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የገጸ ምድር ውሃ መጠን በተለያዩ ተፋሰሶች ላይ እንደሚጨምርም ገልጸዋል። በዚህም ኦሞ ጊቤ፣ ስምጥ ሸለቆ፣ የላይኛውና መካከለኛው አዋሽ፣መካከለኛና ታችኛው አባይ፣ ገናሌ ዳዋ እና ዋቤ ሸበሌ ተፋሰሶች የተሻለ እርጥበት እንደሚያገኙ ይጠበቃል ብለዋል። በዚህም የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የውሃ ማጠራቀሚያዎችን በመጠቀም የውሃ መጠናቸው ከፍ እንዲል ያደርጋል ብለዋል። ከዚሁ ጋር በተያያዘ በአንዳንድ የአገሪቱ ክፍሎች አሁንም ከፍተኛ የቀን ሙቀት እንደሚቀጥል ገልጸዋል። በዚህም በጋምቤላ፣ አፋር፣ ሶማሌ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝና ምዕራብ አማራ አካባቢዎች የቀኑ ከፍተኛ ሙቀት ከ33 እስከ 37 ነጥብ 2 ዲግሪ ሴልሺየስ ሊደርስ እንደሚችል የትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ ተብሏል።
ኢንስቲትዩቱ አራተኛውን የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስራ ሊያስጀምር ነው
Mar 3, 2026 111
ዳንቦያ፤ የካቲት 24/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣ ከንባታ ዞን አራተኛውን ዘመናዊ የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር የመትከል ተግባርን በማጠናቀቅ ስራ ለማስጀመር የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ እንደሚገኝ አስታወቀ። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ እንደገለጹት፤ ኢንስቲትዩቱ በክልሉ ከንባታ ዞን ዳንቦያ ወረዳ ዳቶ ዳርሀቦራ ተራራ ላይ ነው ዘመናዊ የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳሩን የተከለው። ራዳሩ በ250 ኪሎ ሜትር ራዲየስ ውስጥ ያለን የአየር ሁኔታ መረጃ የመሰብሰብ አቅም ያለው ሲሆን፣ የትንተናና የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራዎችን በተሻለ ጥራት ለመከወን ያስችላል ብለዋል። በ14 ሜትር ከፍታ ላይ የተተከለው ይህ ራዳር የዝናብ መጠንን፣ የንፋስ ፍጥነትን፣ የዳመና እንቅስቃሴንና ዝናብ ያዘለ አውሎ ነፋስን የመሳሰሉ መረጃዎችን ከርቀት በመቃኘት ለዋናው የዳታ ማዕከል መረጃ ያስተላልፋል ብለዋል። ይህ የራዳር ጣቢያ በኢትዮጵያና በፊንላንድ መንግሥታት ድጋፍ 13 ሚሊዮን ዩሮ በሚጠጋ በጀት ወደ ሥራ ከሚገቡ ፕሮጀክቶች አንዱ መሆኑን የገለፁት ዳይሬክተሩ፤ አገልግሎቱን በቴክኖሎጂ ለማዘመንና የተሳለጠ መረጃ ለማቅረብ ትልቅ ፋይዳ እንዳለውም አብራርተዋል። በፕሮጀክቱ የተጠቀሰውን ጨምሮ አራት የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳሮች፣ 10 የአየር ብክለት መከታተያ ጣቢያዎች፣ 10 የመብረቅ መከታተያና ሌሎች የተቀናጁ የሚቲዎሮሎጂ መሠረተ ልማትን የመገንባት ሥራን ያካተተ ነው ብለዋል። ኢንስቲትዩቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ በ12 ስልታዊ ቦታዎች ላይ የራዳር ጣቢያዎችን ለመትከል እቅድ መያዙን ጠቁመው፤ አራተኛውን ጣቢያ በማጠናቀቅ የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎቱን የማሳደግ አቅሙን አንደሚያጠናከር አስረድተዋል። ራዳሩ በተተከለበት አካባቢ የኃይል መቆራረጥም ሆነ የመረጃ ልውውጥ እንዳይቋረጥ የፀሐይ ብርሃን ኃይል (ሶላር ኢነርጂ) እየተገጠመ ይገኛል ብለዋል። የፕሮጀክቱን የመጨረሻ ምዕራፍ ለመጎብኘት በስፍራው የተገኙት በፊንላንድ ኤምባሲ የትብብር ዘርፍ ኃላፊ ቶሚ ሳርኪኦጃ መንግሥታቸው የኢትዮጵያን ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በመደገፉ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ ነው
Mar 3, 2026 83
ነጌሌቦረና፤የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ ኩልሌ ሸና እንደገለጹት፤ ዞኑ ቆላማና ዝናብ አጠር በመሆኑ በየጊዜው የሚያጋጥመውን የእንስሳት መኖ እጥረት በዘላቂነት ለመቋቋም ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። ለዚህም በዘንድሮው የበጋ ወቅት ሕብረተሰቡን በማሳተፍ 105 ተፋሰሶችን መሠረት ያደረገ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል። በዞኑ በሁሉም ወረዳዎች በሚገኙ ተፋሰሶች ላይ የሚካሄደው የተቀናጀ የልማት ሥራ ከ52 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት የሚያካልል መሆኑን አቶ ኩልሌ ጠቁመዋል። ከዚህ ውስጥ በሰው ሰራሽ ጫና እና ከልክ ያለፈ ግጦሽ የተራቆተ ከ38 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ተከልሎ መልሶ እንዲያገግም እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በተከናወነው እንቅስቃሴ 24 ሺህ 430 ሄክታር የግጦሽ መሬት ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተከልሎ እንዲያገግም የተደረገ ሲሆን፣ ይህም መኖን በዘላቂነት ለማግኘት የሚደረገውን ጥረት ያግዛል። ከተፈጥሮ ግጦሽ በተጨማሪም በክረምትና በበጋ መስኖ የታገዘ የመኖ ልማት ለማስፋፋት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ምክትል ኃላፊው አስታውቀዋል። በዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ከተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት መካከል የአፈርና የድንጋይ እርከን እንዲሁም የጎርፍ መፋሰሻ ቦይ ግንባታ እየተከናወነ ሲሆን የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ዝግጅትንም ጠቅሰዋል። በነዚህ የልማት ሥራዎች ላይ አርሶና አርብቶ አደሮች፣ የወጣቶችና የሴቶች አደረጃጀቶች በንቃት ተሳትፈዋል። ከዚህም ባለፈ በበልግና በክረምት የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማዘጋጀት ሥራ እየተከናወነ መሆኑ ተገልጿል። የሊበን ወረዳ የጎቢቻ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ወርቁ አለባቸው በሰጡት አስተያየት፤ አካባቢያቸው ዝናብ አጠር በመሆኑ በተደጋጋሚ ለሚከሰተው የእንስሳት መኖ እጥረት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት ከደረሰባቸው ጉዳት በመማር አሁን ላይ በአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ላይ በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛው የቀበሌው ነዋሪ አቶ አልዬ ኢብራሂም በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ አሻራ እና የእንስሳት መኖ ልማት ለአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ የህልውና ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰው፤ ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም በአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ላይ ቅድሚያ በመስጠት እንደሚሳተፉ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ ናቸው
Mar 2, 2026 105
አዲስ አበባ፤ የካቲት 23/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና አውደ ጥናት በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት እንዳሉት የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በዓለም ደረጃ የአካባቢ መራቆትን፣ የብዝሃ ህይወት መመናመንን እንዲሁም በትልልቅ የውሀ አካላት ላይ እየደረሱ ያሉ ጉዳቶችን ለመከላከል ድጋፍ የሚያደርግ ዓለም አቀፍ ተቋም ነው። ተቋሙ ለሚቀጥሉት አራት ዓመታት የሚሆን ፕሮግራም ተግባራዊ እንደሚያደርግ ገልጸው የአውደ ጥናቱ ዓላማ ከዚህ ቀደም የተተገበሩ ፕሮግራሞችን ለመገምገም መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ እና የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ረገድ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ተግባራዊ መደረጋቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በእነዚህ ስራዎች አማካይነት እውቅና እያገኘችበት እንደምትገኝም ገልጸዋል። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ በበኩላቸው የምስራቅ አፍሪካ ሰፊ የተፈጥሮ ሀብት እና እምቅ አቅም እንዳለው ጠቅሰው፥ ይሁን እንጂ እንደ ብዝሃ-ህይወት መጥፋት፣ የመሬት መራቆት እና ብክለት ያሉ ፈተናዎች የተደቀኑበት ቀጣና ነው ብለዋል። በመሆኑም ቀጣናዊና፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት በአየር ንብረት ለውጥ የሚደርሱ ጫናዎችን ለመቋቋም በትብብር መሥራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በተለያዩ መንገዶች የገንዘብ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ከዘላቂ ልማትና ከአረንጓዴ የኢኮኖሚ እድገት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ እርምጃዎችን እየወሰደች ነው
Mar 2, 2026 114
አዲስ አበባ፤ የካቲት 23/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ከዘላቂ ልማትና ከአረንጓዴ ኢኮኖሚ እድገት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ እርምጃዎችን እየወሰደች መሆኑን የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና አውደ ጥናት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማትና በታዳሽ ኃይል ለዓለም የስኬት አርዓያ ሆናለች -የሮማኒያ አምባሳደር የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት፥ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የሥነ-ሕይወት መጥፋት እና ብክለት በምድራችን የአካባቢ ደህንነት፣ የምግብ ዋስትና እና የልማት ጉዞ ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይ በምስራቅ አፍሪካ የሚከሰቱ ድርቅና የአካባቢ መራቆት በማህበረሰቡና በስርዓተ ምህዳሩ ላይ አስከፊ ጉዳት እያስከተሉ እንደሚገኙ ገልጸዋል። አካባቢን መጠበቅና የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የህልውና ጉዳይና የብልጽግና መሰረት መሆኑን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመከላከል ለአፍሪካና ለዓለም ምሳሌ የሚሆን አኩሪ የአረንጓዴ ልማት ተግባራትን እያከናወነች እንደምትገኝ ተናግረዋል። ከዘላቂ ልማትና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ከመገንባት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎቿ ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በሰባት ዓመታት ውስጥ ብቻ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ታላቅ የደን ልማት ለዓለም ማሳየቷንም አንስተዋል። እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ያሉ የታዳሽ ሃይል ልማት ፕሮጀክቶች፣ የከተሞች የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ ልማት፣ የሌማት ትሩፋት፣ የበጋ መስኖ ስንዴ እና ሌሎችም የልማት ኢኒሼቲቮች ከራሷ አልፎ ለቀጣናው ዘላቂ ዕድገት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል። የአውደ ጥናት የምክክር መድረኩ በአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ዙሪያ የትብብር ሥራዎችን በማስፋት የጋራ ዕድገትን ለማረጋገጥ የሚበጁ ምክር ሀሳቦችን ለማመንጨት እንደሚረዳ አንስተዋል። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ በበኩላቸው፤ ምስራቅ አፍሪካ ሰፊ የተፈጥሮ ሀብት እና እምቅ አቅም እንዳለው ጠቅሰው፥ ይሁን እንጂ እንደ ብዝሃ-ህይወት መጥፋት፣ የመሬት መራቆት እና ብክለት ያሉ ፈተናዎች የተደቀኑበት ቀጣና ነው ብለዋል። በመሆኑም ቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት በአየር ንብረት ለውጥ የሚደርሱ ጫናዎችን ለመቋቋም በትብብር መሥራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል።
አዲሱ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ እና አወጋገድ አዋጅ 1383/2017 "ሁሉንም ዓይነት ፕላስቲኮች" ሙሉ በሙሉ አግዷል?
Feb 28, 2026 158
የኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የፕላስቲክ ብክለትን በመቀነስ የአካባቢን ደህንነት ለማረጋገጥ ያለመውን አዲሱን የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ እና አወጋገድ አዋጅ 1383/2017 ወደ ትግበራ ማስገባቱ ይታወቃል። ይሁን እንጂ፣ የዚህን አዋጅ መውጣት ተከትሎ በማህበራዊ ሚዲያ አማራጮች ላይ ማህበረሰቡን የሚያሳስቱ መረጃዎች በስፋት እየተዘዋወሩ ይገኛሉ። በመሆኑም በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በስፋት እየተሰራጩ ያሉትን ዋና ዋና አሳሳች መረጃዎች በመለየት፤ ከአዋጁ፣ ከኃላፊዎች ማብራሪያ እና ይፋዊ መግለጫዎች ጋር በማገናዘብ መረጃ ማጣራት ተደርጓል። የተሳሳተ መረጃ፡- "ማንኛውም ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ እንዳይመረት፣ እንዳይገባ እና እንዳይሸጥ ሙሉ በሙሉ ታግዷል" እውነታው፡- አዋጁ ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ ፕላስቲኮችን በሙሉ አልከለከለም። በህጉ መሰረት ሙሉ በሙሉ የተከለከሉት ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውሉ "ስስ የፕላስቲክ ከረጢቶች (ፌስታል)" ብቻ ናቸው። የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 በግልጽ እንደሚያስቀምጠው፤ “ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ እንዲመረት፣ ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገባ ወይም ጥቅም ላይ እንዲውል መመሪያ ሊወስን ይችላል” ይላል። ይህም ማለት እንደየአስፈላጊነቱ የሚፈቀዱ ፕላስቲኮች አሉ። ይህንን ጉዳይ በተመለከተ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገጹ በሰጠው ማብራሪያ፤ የፕላስቲክ ማሸጊያ ማለት እቃዎችን ከብክለት ለመከላከል ወይንም ከሌላ ነገር ጋር እንዳይቀላቀል ለማድረግ የሚጠቅም መሆኑን ጠቅሶ፤ የምግብ፣ የባልትና ውጤቶች፣ የላውንደሪ አገልግሎት እና ሌሎች ምርቶችን ለማሸግ የሚውሉ የፕላስቲክ ማሸጊያዎች በአዋጁ የተፈቀዱ መሆናቸውን አረጋግጧል። የእነዚህ ማሸጊያዎች አወጋገድ በቀጣይ በሚወጡ መመሪያዎች የሚመራ ይሆናል። በተጨማሪም የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሌሊሴ ነሜ(ዶ/ር) ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት(ኢዜአ) በሰጡት ማብራሪያ፤ አዋጁ የፕላስቲክ ምርቶችን ሙሉ ለሙሉ የሚከለክል እንዳልሆነ በግልጽ አረጋግጠዋል። የተሳሳተ መረጃ፡- "የቁጥጥር ስራውን የሚያከናውነውና እርምጃ የሚወስደው የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ብቻ ነው" እውነታው፡- አዋጁን የማስፈጸም የበላይ ኃላፊነት የተሰጠው ለአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን እና ለክልል የአካባቢ ጥበቃ ቢሮዎች መሆኑ እውነት ቢሆንም፤ የቁጥጥር ስራው ግን በባለስልጣኑ ብቻ የሚከወን አይደለም። ህጉ ወደ መሬት ወርዶ ተግባራዊ ሲደረግ፣ በየዕለቱ ህገ-ወጥ ስስ የፕላስቲክ ከረጢቶችን በሚያመርቱ፣ በሚያስገቡ እና በሚጠቀሙ አካላት ላይ ክትትል የሚያደርጉት እና የቁጥጥር እርምጃ የሚወስዱት የፖሊስ እና የደንብ ማስከበር አካላት መሆናቸውን ዋና ዳይሬክተሯ አብራርተዋል። በመሆኑም ህዝቡ እና የንግዱ ማህበረሰብ የቁጥጥር ስራው በጸጥታና ደንብ አስከባሪ አካላት ጭምር የሚተገበር መሆኑን ሊገነዘቡት ይገባል። ህብረተሰቡ በማህበራዊ ሚዲያ የሚናፈሱ ያልተረጋገጡ አሳሳች መረጃዎችን ባለመቀበል የፕላስቲክ አጠቃቀምን በተመለከተ የሚወጡ መመሪያዎችን በቀጥታ ከባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ይፋዊ ገጾች እና ከታማኝ ምንጮች ብቻ እንዲወስድ ይመከራል።
የፕላስቲክ ከረጢት ክልከላን ለማሳካት ህብረተሰቡ እያደረገ ያለው ተሳትፎ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል
Feb 27, 2026 153
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦ህብረተሰቡ የፕላስቲክ ከረጢቶች ላይ የተጣለውን ክልከላ ተግባራዊ ለማድረግ እያበረከተ ያለውን አስተዋፅኦ አጠናክሮ እንዲቀጥል የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ጥሪ አቀረቡ። ባለስልጣኑ ከአምራቾች ጋር በመሆን ተኪ ምርቶች በስፋት ለተጠቃሚ ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑንም ተናግረዋል። በሀዋሳ በፕላስቲክ ከረጢት ምትክ አማራጭ ምርቶችን የመጠቀም ልምድ እየዳበረ ነው የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ እና አወጋገድ አዋጅ 1383/2017 ከጥር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የፕላስቲክ ከረጢት ማምረት፣ ወደ ሃገር ማስገባት፣ መሸጥና መጠቀም ላይ ሙሉ ክልከላ ማድረጉ ይታወቃል። የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት፤ አዋጁ በየጊዜው እየጨመረ የመጣውን የህዝብ ቁጥር፣ የከተሞች መስፋፋት እንዲሁም የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ስርዓት መዘርጋትን መነሻ በማድረግ የተዘጋጀ ነው። በለውጡ ዓመታት የተሰሩ የኮሪደርና ወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎች ፅዳት ማዕከል ያደረጉ እንዲሆኑ በማስቻል ንፁህና ፅዱ ለማድረግ አሁን ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር የተጣጣመ አዋጅ ማዘጋጀት ማስፈለጉን ተናግረዋል። አዋጁ ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውሉ የፕላስቲክ ከረጢቶች(በተለምዶ ፌስታል የሚባሉት) ላይ ሙሉ በሙሉ ክልከላ ያደረገ አዋጅ መሆኑን አንስተዋል። አዋጁ የበርካታ ሀገራት ልምድን ከመቀመር ባለፈ የፕላስቲክ ከረጢቶች በጤና ላይ የሚያደርሱትን አሉታዊ ተፅዕኖ ታሳቢ በማድረግ መዘጋጀቱን ተናግረዋል። እነዚህ ፕላስቲክ ከረጢቶች ለካንሰር፣ ለአዕምሮ እድገት ውስንነት እና ለመተንፈሻ አካላት ህመሞች ምክንያት መሆናቸውን አንስተው፤ የአፈር ለምነትን፣ ውሃ አየር እና በእንስሳት ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርስ እንደሆነ እንዲሁም የምግብ ዋስትናንና ሉዓላዊነትንም እንደሚያደናቅፍ አመልክተዋል። የፕላስቲክ ከረጢት አጠቃቀም ልምድን ለመቀየር ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውሉ ፕላስቲክ ከረጢቶች ሙሉ በሙሉ መከልከላቸውን አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅትም በአብዛኞቹ የሀገሪቷ አካባቢዎች ሕጉ ተፈፃሚ መሆኑን ጠቅሰው፤ ጥብቅ የክትትል ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የአዋጁ ትግበራ የጊዜ ገደብ ተራዝሟል የሚል ሃሰተኛ መረጃ እየተሰራጨ እንደሚገኝ ጠቁመው፤ ህብረተሰቡ በዚህ የተሳሳተ መረጃ ሳይዘናጋ ለአዋጁ ተፈፃሚነት የበኩሉን ሚና መወጣቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል። ባለስልጣኑ ከአምራቾች ጋር በመሆን አማራጭ ምርቶች በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲቀርቡ እየሰራ መሆኑን አንስተው፤ በዚህም አብዛኛው ኢንዱስትሪዎች ምርቶችን በስፋት እያመረቱ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ አሁንም ምርትን በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ መስራት እንደሚጠይቅ ጨምረው አስታውቀዋል። በአካባቢ ላይ የሚደርሱ ብክለቶች ዙሪያ ጥቆማ የሚያደርሱበት እንዲሁም ቅሬታ የሚያቀርቡበት የዲጂታል ስርዓት ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር እየተዘረጋ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በክልሉ በተያዘው የበጋ ወራት ከ64 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የአፈርና የውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት እየተከናወነ ነው
Feb 27, 2026 115
ጋምቤላ፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በተያዘው የበጋ ወራት ከ64 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የአፈርና የውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት በመከናወን ላይ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮ ኃላፊው አድሮው ቱት ለኢዜአ እንደገለጹት ምርታማነትን ለማሳድግ በበጋው ወራት የተጠናከረ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። በክልሉ በሚገኙ ሶስቱም ዞኖች የአፈርና ውሃ ጥበቃ የተፋስ ልማት ስራዎች በተጠናከረ መልኩ እየተከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የተፋሰስ ልማት ስራዎች በክልሉ በሚገኙ 13 ወረዳዎች በተመረጡ 101 ተፋሰሶች በመደበኛና በፕሮጀክቶች ከ64ሺህ ሄክታር በላይ በሚሸፍን መሬት ላይ እየተከወነ መሆኑን ተናግረዋል። በተፋሰስ ልማት ስራው ከአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች በተጓዳኝ ባለፈው ክረምትና ከዚያ በፊት በአረንጓዴ አሻራ ልማት ለተተከሉ ችግኞች እንክብካቤ እየተደረገ እንደሆነም አክለዋል። በክልሉ በበጋው ወራት እየተካሄደ ያለውን የአፈርና ውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት ስራዎች በመጪው የአረንጓዴ አሻራ ልማት ስነ-ህይወት ለማላበስ በ66 የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች የማፍላት ስራ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በመጪው ክረምት በሚከናወነው ለአረንጓዴ አሻራ ልማት መርሃ ግብር ከሚዘጋጁት ችግኞች መካከል ከ8 ነጥብ 2 ሚሊየን በላይ ከደንነት በተጨማሪ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው መሆናቸውን ኃላፊው ገልጸዋል።
የመሬት እንቅስቃሴ አደጋዎችን ለመቀነስ የመከታተያ ማዕከላት ማስፋፋት ያስፈልጋል - የዘርፉ ምሁራን
Feb 26, 2026 168
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2018(ኢዜአ)፦ የመሬትመንቀጥቀጥና የእሳተ ገሞራ አደጋዎችን ለመቀነስ የመከታተያ ማዕከላት ማስፋትና የህዝብን ግንዛቤ ማሳደግ እንደሚያስፈልግ የዘርፉ ምሁራን ገለጹ። የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ "የመሬት መንቀጥቀጥና የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ አደጋ በኢትዮጵያ ስጋትና መፍትሔዎች" በሚል መሪ ሃሳብ የውይይት መድረክ እያካሄደ ነው። በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ በተሰናዳው መድረክ የታደሙት የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ተከተል ዮሀንስ፤ ምሁራን በሀገራቸው ጉዳይ ያላቸውን ሚና ማላቅ የሚያስችል ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። ለዚህም በተለያዩ ሀገራዊ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥናትና ምርምር በማካሄድ ለሕትመትና ተደራሽነት እንዲበቁ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም በኢትዮጵያ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የሚኖራቸውን መፍትሔ አመላካች የጥናትና ምርምር ሥራ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የጂኦ-ፊዚክስ ስፔስ ሳይንስና አስትሮኖሚ ተቋም የመሬት መንቀጥቀጥ ሳይንስ ተመራማሪ ፕሮፌሰር አታላይ አየለ፤ የመሬት እንቅስቃሴ በተፈጥሮ ላይ ተጽዕኖ ያሳድራል ብለዋል። በመሬትና በብዝኅ ህይወት ላይ የሚፈጥረው የገጽታ ለውጥም በህዝብ ባህላዊና ኢኮኖሚያዊ አኗኗር ሥርዓት ከፍተኛ ጫና እንደሚያሳድር ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የሚከሰቱ የመሬት እንቅስቃሴዎችንም በመከታተል በተለያዩ ጊዜያት ህዝቡን የማስገንዘብ ስራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የመሬት መንቀጥቀጥና የእሳተ ገሞራ ፍንዳታ አደጋዎችን አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠትም የማዕከላትን መረጃ ማጠናቀር አቅም ማጎልበት እንደሚያስፈልግ አንስተዋል። የምህንድስና የመወያያ ሃሳብ ያቀረቡት የጂኦቴክኒክ ኢንጅነሪንግ ተመራማሪው ፕሮፌሰር አስራት ወርቁ በበኩላቸው፤ የመሬት እንቅስቃሴ አደጋዎችን ለመቀነስ የግንባታ ጥራትን ማስጠበቅ ይገባል ብለዋል። የህንፃና ተያያዥ መሰረተ ልማት ገንቢ ተቋማትና መሃንዲሶችም ከመሬት ሳይንስ ተመራማሪዎች ጋር በመቀናጀት መስራት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የመሬት መንቀጥቀጥ ማህበራዊ ገጽታን አስመልክቶ ጽሁፍ ያቀረቡት ፕሮፌሰር ተገኝ ገብረእግዚአብሔር፤ የስምጥ ሸለቆ የከተሜነት መስፋፋት ለመሬት እንቅስቃሴ አደጋ ተጋላጭነትን ከፍ ያደርጋል ብለዋል። ለዚህም የሀገራትን ተሞክሮ በመቀመር የቅድመ ማስጠንቀቂያና የመሠረተ ልማት ጥራትን ማጠናከር እንደሚገባ አስረድተዋል።
ለብሔራዊ ፓርኮችና ጥብቅ ሥፍራዎች ልማት የተሰጠው ትኩረት ከቱሪዝም ዘርፉ የበለጠ ለመጠቀም ያስችላል
Feb 26, 2026 301
ባህር ዳር ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡-ለብሔራዊ ፓርኮችና ጥብቅ ሥፍራዎች ልማት የተሰጠው ትኩረት ከቱሪዝም ዘርፉ የበለጠ ለመጠቀም የሚያስችል መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ገለጹ። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የኢትዮጵያ ዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ በሀገሪቱ 29 ብሔራዊ ፓርኮችና 87 ዓይነት ጥብቅ ስፍራዎች ይገኛሉ ብለዋል። የጥብቅ ስፍራዎችን ማስፋፋት ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና የአካባቢ ጥበቃ ፋይዳው የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል። እንደ ጨበራ ጩርጩራ፣ አዋሽ እና ባሌ ብሔራዊ ፓርኮች ያሉ ሥፍራዎች ላይ የተሰሩ የልማት ሥራዎች ለቱሪዝም ዘርፉ ዕድገት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑንም እንዲሁ። በጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ የሚታየውን ልዩ የዱር እንስሳት እንቅስቃሴ ለቱሪዝም መስህብነት ለማዋል የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ እንደሆነም ነው ያብራሩት። በፓርኮች ውስጥ የሚስተዋሉትን ልቅ የእንስሳት ግጦሽ፣ የደን ጭፍጨፋ፣ ሕገ-ወጥ አደንና የእርሻ መስፋፋት ችግሮችን ለማስወገድ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ብለዋል። መንግስት የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማስፋት ረገድ የሰጠው ልዩ ትኩረት ዘርፉ በፍጥነት እያደገ እንዲመጣ ማስቻሉንም ገለጸዋል። የአማራ ክልል አካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን ኃላፊ ተስፋሁን ዓለምነህ በበኩላቸው፤ በክልሉ የእንሰሳትና የብዝሃ ሕይወት የመጠበቅ ስራ ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ መልኩ እየተሰራ ነው ብለዋል። በሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ የሚስተዋሉ ሰደድ እሳት፣ ህገወጥ እርሻ፣ ደን ጭፍጨፋ፣ ሕገ-ወጥ አደንና መሰል ተግባራትን ሕብረተሰቡን በማስተባበር የመጠበቅ ስራ እየተሰራ መሆኑንም አስታውቀዋል። ፓርኩ ለአካባቢው ማሕብረሰብ ያለውን ጠቀሜታ ግምት ውስጥ በማስገባት ቀደም ሲል 136 ስኩዌር ኪሎ ሜትር የነበረውን የፓርኩ ይዞታ ወደ 412 ስኩዌር ኪሎ ሜትር እንዲሰፋ መደረጉን አስታውሰዋል። ፓርኩን የማስፋት ስራ በዩኔስኮ መመዝገብ ስላለበት ይህንኑ ተግባር እውን ለማድረግ በጥናት ላይ መሰረት ያደረገ ሰነድ ተዘጋጅቶ መቅረቡን ተናግረዋል። የደባርቅ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት አስማማው ዘገየ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ዩኒቨርሲቲው ከመማር ማስተማር ስራው በተጓዳኝ በምርምርና በማሕበረሰብ አገልግሎት ፓርኩን እያገዘ ነው። የቱሪዝምና ቅርስ አስተዳደር የትምህርት ክፍል በመክፈት ተማሪዎች በተግባር የታገዘ ትምህርት እንዲወስዱ ከማድረግ ባሻገር ከተለያዩ የዓለም ሀገራት ጋር ግንኙነት በመፍጠር ሃብቱን የማስተዋወቅ ስራ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። በሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ቀደም ሲል የተካሄደው የይዞታ ማስፋት ስራ የአካባቢውን ማሕበረሰብ የበለጠ በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ያደረገ ነው ያሉት ደግሞ የፓርኩ የሕግ ማስከበር ቡድን መሪ ሲሳይ ሰለሞን ናቸው። በማስፋት ስራውም ቀደም ሲል ያልተካተቱ ሥፍራዎች መካተታቸውን ጠቅሰው፤ ለዩኔስኮ የቀረበው ሰነድ ሲፀድቅ የፓርኩን ዓለም አቀፍ እውቅና ያሳድጋል ብለዋል።
በሀዋሳ በፕላስቲክ ከረጢት ምትክ አማራጭ ምርቶችን የመጠቀም ልምድ እየዳበረ ነው
Feb 26, 2026 319
ሀዋሳ ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በሀዋሳ ከተማ በፕላስቲክ ከረጢት ምትክ አማራጭ ምርቶችን የመጠቀም ልምድ እየዳበረ መምጣቱን የከተማ አስተዳደሩ አካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ቁጥጥር ጽህፈት ቤት ገለፀ፡፡ በደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 መሠረት እንደ ሀገር ከጥር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የፕላስቲክ ከረጢት ማምረት፣ ወደ ሀገር ማስገባት፣ መሸጥና መጠቀም ላይ ክልከላ ተደርጓል፡፡ አዲስ አበባ በንፅህና አጠባበቅ ረገድ እያከናወነች ያለው ሥራ በአርዓያነት ይጠቀሳል ባልተገባ መልኩ የሚጣሉ የፕላስቲክ ከረጢቶች /ፌስታል/ አካባቢን በመበከል፣ የውሃ መስመሮችን በመዝጋት፣ በተለይ ሳይበሰብሱ ለብዙ ዓመታት በመቆየት የስነ ምህዳር ጠንቅ እንደሆኑ ሳይንሳዊ ምርምሮች ያወሳሉ። በኢትዮጵያ የፕላስቲክ ከረጢት አጠቃቀምን ለመገደብና ለመከልከል ባለፉት ዓመታት በርካታ ጥረቶች ሲደረጉ የቆዩ ሲሆን ክልከላው በዋናነት የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስና የህዝብን ጤና ለመጠበቅ ያለመ መሆኑም ይታወቃል። ይህንን ተከትሎ በሀዋሳ ከተማም ክልከላው ተግባራዊ እየተደረገ ሲሆን በህብረተሰቡ ዘንድ በፕላስቲክ ከረጢት ምትክ አማራጭ ምርቶች የመጠቀም ልምድ እየዳበረ መምጣቱን የጽህፈቱ ቤት ኃላፊ አቶ ዳንኤል ሹምባሻ ለኢዜአ ገልጸዋል፡፡ ጽህፈት ቤቱም ክልከላውን ከማስተግበር ጎን ለጎን ምትክ ምርቶች በስፋት ለሕብረተሰቡ እንዲቀርቡ እየሰራ እንደሚገኝ ነው የተናገሩት። በአሁኑ ወቅት በከተማዋ 15 ድርጅቶች ምትክ የወረቀት ከረጢቶችን በማምረት ሥራ ላይ በመሰማራታቸው አዋጁን ከመተግበር ባለፈ ለዜጎች የስራ እድል መፍጠር ችለዋል ብለዋል። የኤሊያና ፔፐር ፓኬጂንግ ኤንድ ማኑፋክቸሪንግ ሥራ አስኪያጅ አቶ ደረጀ ሞገስ በበኩላቸው፤ ድርጅታቸው የወረቀት ከረጢቶችን በስፋት የማምረት ስራ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡ አዋጁ ስነ ምሕዳሩን ከመጠበቅ ባለፈ በዘርፉ ተጨማሪ የገበያ ዕድል በማስገኘት ሰፊ አስተዋጽኦ አበርክቷል ነው ያሉት። በአሁኑ ወቅትም 85 ወጣቶችን በማሰልጠን የስራ እድል ለመፍጠር የተቻለ ሲሆን በቀን እስከ 15 ሺህ የወረቀት ከረጢቶችን እያመረቱ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በሱፐር ማርኬት ሥራ ላይ የተሰማሩት ወይዘሮ ፀሐይ ይርዳው በበኩላቸው፤ የጨርቅ ከረጢቶችና ካርቶኖችን በመጠቀም ደንበኞቻቸውን እያስተናገዱ እንደሚገኙ ይገልፃሉ። ከዚሁ በተጨማሪም ማህበረሰቡ አምኖበት የወረቅ ምርቶቹን እንዲጠቀም ለማድረግም ግንዛቤ የመፍጠር ስራ እየሰሩ መሆኑን ነው ያነሱት። በሆቴል ሥራ ላይ የተሰማሩት ወይዘሮ ልደት ማሩፋ፤ የፕላስቲክ ከረጢት ክልከላው ሀዋሳን ፅዱ ከማድረግ ባለፈ ሀይቁን ከብክለት ሥጋት ነፃ የሚያደርግ በመሆኑ በደስታ እንደተቀበሉት ገልፀዋል፡፡ ለቤታቸው በሚሸምቱት ዕቃም ሆነ በሆቴል አገልግሎታቸው አማራጭ ምርቶችን ብቻ እየተጠቀሙ መሆኑን ተናግረው የክልከላ አዋጁ ተግባራዊ እንዲሆንና ፅዱ ከተማን ለመፍጠር ሁሉም መተባበር እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማትና በታዳሽ ኃይል ለዓለም የስኬት አርዓያ ሆናለች -የሮማኒያ አምባሳደር
Feb 25, 2026 157
አዲስ አበባ፤ የካቲት 18/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማትና በታዳሽ ኃይል ለዓለም የስኬት አርዓያ ሆናለች ሲሉ በኢትዮጵያ የሮማኒያ አምባሳደር ጁሊያ ፓታኪ ገለጹ። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ቀጣናውን በሀይል በማስተሳሰር ረገድም ጉልህ ፋይዳ እንዳለውም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጭነት ባለፉት ዓመታት በተገበረችው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መትከል ችላለች። ይህ ተግባርም የዓለም የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል የተስተካከለ ምህዳርን ለመፍጠር ጉልህ ሚና አለው። ኢትዮጵያ በዚህ ተግባሯም ዓለም አቀፍ እውቅናዎችን አግኝታለች። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት በኢትዮጵያ የሮማኒያ አምባሳደር ጁሊያ ፓታኪ የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት ማጠናከር የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ወደ ልማት ለማሳደግ እየሰራች መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ ስኬቶች ሀገሪቷን በዓለም ላይ እውቅና እያስገኘላት መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ድንቅ የአካባቢ ጥበቃ ስራ መሆኑን ጠቁመዋል፤የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መረጃዎችን እያስፋፋን ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ እየተገበረችው ያለው የአረንጓዴ አሻራ ስኬቶች ሀገሪቷን በአረንጓዴ ልማት፣ በታዳሽ ሀይል ስራዎች ለሌሎች ሀገራት አርዓያ አድርጓታል ብለዋል። አምባሳደሯ አክለውም ኢትዮጵያ በልማት ጎዳና ላይ መሆኗን ጠቁመው፤ በአዲስ አበባ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እየተመዘገቡ ያሉ የልማት ውጤቶች የሚደነቁ መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህ የልማት እንቅስቃሳም በሌሎች የክልል ከተሞች እየተስፋፋ መሆኑን ጠቁመዋል። የኮሪደር እና የወንዝ ዳርቻ ልማቶችን ጨምሮ በከተማዋ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች አዲስ አበባን እውነተኛ የአፍሪካ መዲናነቷን በተግባር ያረጋገጡ ናቸው ብለዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ትልቅ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያለው በአፍሪካ ልዩ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። ግድቡ ቀጣናውን በሀይል በማስተሳሰር ረገድም ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል።
የበልግ እርሻ እንቅስቃሴን ቀድመው የሚጀምሩ አካባቢዎች፣ በሚቀጥሉት ስምንት ቀናት የሚኖረውን የእርጥበት አየር ሁኔታ በአግባቡ ሊጠቀሙበት ይገባል
Feb 23, 2026 158
አዲስ አበባ፤ የካቲት 16/2018(ኢዜአ)፦የበልግ እርሻ እንቅስቃሴን ቀድመው የሚጀምሩ አካባቢዎች፣ በሚቀጥሉት ስምንት ቀናት የሚኖረውን የእርጥበት አየር ሁኔታ በአግባቡ ሊጠቀሙበት እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አሳሰበ። ኢንስቲትዩቱ ከየካቲት 14 እስከ 21 ቀን 2018 ዓ.ም የሚኖረውን የአየር ሁኔታ አስመልክቶ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፤ በሚቀጥሉት ቀናት በበልግ አብቃይ አካባቢዎች ላይ አንጻራዊ የእርጥበት ሁኔታ እንደሚኖር ገልጿል። በተለይም በደቡብ ምዕራብ፣ በደቡብ እና በመካከለኛው ዝቅተኛ አካባቢዎች የሚታየው እርጥበት፤ ለአፈር ዝግጅት፣ ለዘር ዝግጅትና ለዘር መዝራት ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል ብሏል። የሚገኘው እርጥበት ለግጦሽ ሳር በቀል፣ ለቋሚ ተክሎች እድገትና ለሰውና ለእንስሳት የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ለማሻሻል ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለውም አመልክቷል፡፡ በላይኛው አዋሽ፣ በላይኛውና በመካከለኛው ባሮ አኮቦ፣ በኦሞ ጊቤ፣ በስምጥ ሸለቆ እንዲሁም በጥቂቱ በላይኛው ገናሌ ዳዋ ተፋሰሶች ላይ ከመካከለኛ እስከ መጠነኛ ዝናብ እንደሚጠበቅም ተመላክቷል፡፡ በዚህም ምክንያት በተጠቀሱት ተፋሰሶች ላይ መጠነኛ የገፀ-ምድር ውሃ ፍሰት እንደሚኖር ተመላክቷል። በሌላ በኩል የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑት የደቡብ እና የደቡብ ምስራቅ አካባቢዎች ላይ ደረቃማ ቀናት እንደሚስተናገዱ በመግለጫው ተጠቅሷል።
የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የቡና ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ረገድ ትልቅ ለውጥ ፈጥሯል
Feb 23, 2026 300
አዲስ አበባ፤ የካቲት 16/2018(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የቡና ምርትና ምርታማነት በማሳደግ ረገድ ትልቅ ለውጥ ፈጥሯል ሲሉ የዘርፉ ተዋናዮች ገለጹ። ኢትዮጵያ በ2017 በጀት ዓመት 469 ሺህ ቶን ቡና ለዓለም ገበያ በመላክ 2 ነጥብ 65 ቢሊየን ዶላር ገቢ ማግኘቷ የሚታወስ ሲሆን በ2018 ዓ.ም በጀት ዓመት 600 ሺህ ቶን ቡና ወደ ውጪ በመላክ ከሦስት ቢሊየን ዶላር በላይ ለማግኘት አቅዳ እየሰራች ትገኛለች፡፡ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ በዘርፉ የተሰማሩ አካላት በግብርናው ዘርፍ የቡና ምርታማነት ላይ አመርቂ ውጤት ለማስመዝገብ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ ወሳኝ መሆኑን ያረጋግጣሉ። በኦሮሚያ ክልል የቡና አልሚና ላኪ የሆኑት አቶ ፈጠነ የኋላሸት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ በተለይ አረንጓዴ አሻራ ትልቅ አስተዋጾ ማበርከቱን ተናግረዋል ባለፉት ዓመታትም የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር በተከታታይነት መከናወኑ ቡናን ለማምረት ተስማሚ ሥርዓተ ምህዳርና የአየር ሁኔታ እንዲኖር ማስቻሉን ነው ያነሱት። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ በቡና መስክ ላይ የተሰማሩት አንዷለም ፋንታ በበኩላቸው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የቡና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ ትልቅ ለውጥ እያመጣ ነው ብለዋል። ይህም በመሆኑ በአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ላይ የማህበሩ አባላት በስፋት በመሳተፍ ልማቱን እያገዝን እንገኛለን ሲሉ ጨምረው ተናግረዋል። በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የቡና ምርታማነታችንን ለማሳደግ የአካባቢውን የተፈጥሮ ገጽታ መጠበቅ ወሳኝ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በሲዳማ ክልል በቡና አቅራቢነት የተሰማሩት አባተ ኪሾ ናቸው ። አስተያየት ሰጪዎቹ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን እና ዝርያዎችን ለተከላ ለማዘጋጀት የሚያስችላቸውን ተግባር እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡና ማህበር ምክትል ፕሬዚዳንት ዘሪሁን ቃሚሶ በበኩላቸው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ሀገራችን ከቡናው ዘርፍ ማግኘት የሚገባትን ኢኮኖሚያዊ እድገት ለማሳለጥ ትልቅ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። አረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር እንደ ሀገር ማከናወን ከጀመርን በኋላ ከ8 ቢሊየን በላይ የቡና ችግኞች መተከላቸውን አስታውቀዋል።
የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ባህል የማድረግ እንቅስቃሴ
Feb 22, 2026 176
አዲስ አበባ፤የካቲት 15/2018(ኢዜአ)፦በመዲናዋ የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ባህል የማድረግ እንቅስቃሴ በጎ አድራጎት ያለምንም ክፍያና ጎትጓች ለህሊና እርካታ ለሰዎች የሚከወን የዕለት ተዕለት ተግባር ነው። በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በጎ ፈቃድ አገልግሎትን ባህል በማድረግ በቤት እድሳት፣ በደም ልገሳ፣ ማዕድ በማጋራትና በሌሎች ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት በርካታ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የበጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ከፕሎጊንግ ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በእንጦጦ ፓርክ ያዘጋጀው የጽዳትና የበጎ ፈቃድ አገልግሎት መርሃ ግብር ተካሂዷል። በዚህ መርሃ ግብር ላይ ከሁሉም የከተማዋ ክፍለ ከተሞች የተወጣጡ በጎ ፈቃደኞች ተሳትፈዋል። የኮሚሽኑ ምክትል ኮሚሽነር አስራት ንጉሴ በመርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት በጎ ፈቃደኝነት ለራስ የህሊና እርካታን ከመስጠት ባለፈ፣ ጠንካራና የተሳሰረ ማህበረሰብ ለመገንባት ቁልፍ ሚና አለው። የከተማ አስተዳደሩ ይህንን ተግባር የዜጎች የዘወትር ባህል ለማድረግ ባለፉት ዓመታት ትኩረት ሰጥቶ ሲሰራ መቆየቱን ጠቁመው፤ በዚህም በከተማዋ በርካታ ነዋሪዎችን ተጠቃሚ ያደረጉ የበጎ ፈቃድ ስራዎች መከናወናቸውን አስታውቀዋል፡። በአሁኑ ወቅት በሙያቸውና በጉልበታቸው ለሀገራቸው ለህዝባቸው የሚደርስ ማህበረሰብ መፍጠር መቻሉን አንስተው፤ ይህ ንቁ ትውልድ የመፍጠር ሂደት ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። እንደ ፕሎጊንግ ኢትዮጵያ ሁሉ ህብረተሰቡም ሆነ ሌሎች አካላት ብዙ ጥቅም በሚያስገኘው በጎ ፍቃድ በመሳተፍ ሀገሩንና ወገኑን ማገልገል ይገባዋል ብለዋል፡። የፕሎጊንግ ኢትዮጵያ መስራች ፕሮፌሰር ፍሬው ከፍያለው በበኩላቸው፤ አካባቢን መንከባከብ የሁሉም ዜጋ የጋራ ኃላፊነት መሆኑን አስታውቀዋል። ድርጅታቸው ላለፉት አምስት ዓመታት የአካል ብቃት እንቅስቃሴን ከጽዳት ጋር በማቀናጀት (Plogging) በየሳምንቱ የፕላስቲክ ቆሻሻዎችን የመሰብሰብ ዘመቻ ሲያከናውን መቆየቱን አስታውሰዋል። ዝቅ ብሎ ቆሻሻን ማንሳት ለራስ ክብርንና ከፍታን ይሰጣል ያሉት ፕሮፌሰሩ ማህበረሰቡ ይህንን ልምድ እንዲያጠናክር ጥሪ አቅርበዋል። በዕለቱ በጽዳት ዘመቻው ላይ የተሳተፉት በጎ ፈቃደኞች ፍቅር ግርማ እና ካሱ መገርሳ በሰጡት አስተያየት፤ በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ በመሳተፋቸው ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸው፤ በቀጣይም ተሳትፏቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
በዞኑ የለሙ ተፋሰሶች በሌማት ትሩፋት ኢንሼቲቭ ኢኮኖሚያዊ አቅማችንን አሳድገውልናል-ተጠቃሚዎች
Feb 21, 2026 240
አርባ ምንጭ ፤ የካቲት 14/2018 (ኢዜአ)፡- በጋሞ ዞን የለሙ ተፋሰሶች ምርትና ምርታማነትን ከማረጋገጥ ባለፈ በሌማት ትሩፋት ኢንሼቲቭ አኮኖሚያዊ አቅማቸውን ማሳደጉን በዞኑ የሚገኙ ተጠቃሚዎች ገለፁ። በምስራቅ ሸዋ ዞን ከ119 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ዕቀባ ሥራ እየተከናወነ ነው ከተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ወደ ትርፍ ምርት- የአረንጓዴ አሻራ ትሩፋት በዞኑ በበጀት ዓመቱ ወደ 160 ሺህ ሄክታር በሚጠጋ መሬት ላይ የተፋሰስ ልማት እየተከናወነ መሆኑም ተመላክቷል። ተጠቃሚዎቹ እንደገለፁት፤ በዞኑ የለሙ ተፋሰሶች ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ በሌማት ትሩፋት ኢንሼቲቭ ኢኮኖሚያዊ አቅማችንን አሳድጎልናል ብለዋል። አርሶ አደር ሚሊዮን በየነ በዞኑ የቁጫ ወረዳ ነዋሪ ናቸው፤ በአካባቢያቸው ከዚህ ቀደም በተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ስራዎች የተጎዳ መሬት ሲያገግም፣ የጠፋ ምንጭ ዳግም ሲፈልቅ እና የአካባቢው ስነ-ምህዳር ወደ ልምላሜ ሲቀየር በዓይናቸው ተመልክተዋል። አመቺ ባለመሆናቸው ለእርሻ ስራ ጥቅም ላይ ሳይውሉ የቆዩ የእርሻ ማሳዎች ጥቅም ላይ ውለው ወደ ምርታማነት ተቀይረው ሲመለከቱ ደግሞ እውን ሳይሆን ህልም መስሏቸውም ያውቃል። አሁን ላይ በተፋሰስ ልማት ስራው በለማው መሬት ላይም በእንስሳት እርባታና በንብ ማነብ ስራ ላይ በመሰማራት ተጠቃሚ መሆን ጀምረዋል። ለውጡንም በማየታቸው በዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ስራ ላይ ግንባር ቀደም ተሳታፊ መሆን ብቻም ሳይሆን ቤተሰባቸውንም በማስተባበር እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ የ"ነህሚያ የእንስሳት እርባታ ማህበር" ሰብሳቢ ወጣት ህዝቅኤል ኦሎባ የማህበሩ አባላት የተፋሰስ ልማቱ በፈጠረላቸው ጸጋ ተነሳስተው ባለፈው ዓመት በሦስት ላሞች እና በሁለት ኮርማዎች ሥራ መጀመራቸውን አስታውሷል። በተፋሰሱ በለማው ቦታ ላይም መንግስት ባመቻቸላቸው ብድር ለእንስሳት መኖ በማምረት ተጠቃሚነታቸው እየጨመረ መሆኑንም ጠቅሷል። በአሁኑ ወቅት ከላሞቹ አምስት ጥጃዎችን ማግኘታቸውን የጠቀሰው ወጣቱ ለተለያዩ አካላት የወተት ምርት በማቅረብ የገቢ ምንጫቸው ማደጉን አስረድቷል፡፡ በአካባቢው የተከናወነው የተፋሰስ ልማት ጥሩ የስራ ዕድል ይዞልን መጥቷል ያለው ደግሞ በዞኑ ምዕራብ አባያ ወረዳ በአንኮበር ቀበሌ "የጦይሎ ንብ አንቢዎች ማህበር" ሰብሳቢ ወጣት አለማየሁ ቶጋ ነው። ማህበሩ በ2014 ዓ.ም እንደተመሰረተ የሚናገረው አለማየሁ በለማው ተፋሰስ ላይ በአንድ በኩል ንብ እያነቡ በሌላ በኩል የለማው ከባቢ እንዳይጎዳ ጥበቃ በማድረግ ላይ እንገኛለን ብሏል። መንግስት 30 ዘመናዊ የንብ ቀፎዎችን፣ አንድ የማር ማጣሪያ ማሽንና መስሪያ አልባሳት እንዳበረከተላቸው ገልጾ አስፈላጊው የሙያ ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑንም አልሸሸገም። ''በዓመት ከ3 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ ማር እየሸጥን ራሳችንን ከመቻል ባለፈም ቤተሰቦቻችንን እያገዝን እንገኛለን'' ብሏል። የጋሞ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ወርቅነህ ካልሳ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ የተፋሰስ ልማት በተለያየ መልክ የዞኑን ህዝብ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ይገኛል ብለዋል። የተጎዳ መሬትን እንዲያገግም በማድረግ ብሎም ስነ-ምህዳርን በማስተካከል ምርትና ምርታማነት እንዲረጋገጥ በማስቻል የአርሶ አደሮችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እያረጋገጠ ይገኛል ብለዋል። ከተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ጋር በተያያዘ የነዋሪዎች ግንዛቤ እየሰፋ በመምጣቱ ከቴክኖሎጂ አጠቃቀም ጋር ተዳምሮ ምርት በስፋት እየተመረተ ይገኛል ብለዋል። በያዝነው በጀት ዓመትም በ336 ንዑስ ተፋሰሶች 160 ሺህ ሄክታር በሚጠጋ መሬት ላይ የተፋሰስ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውንም አቶ ወርቅነህ ገልጸዋል።
ከተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ወደ ትርፍ ምርት- የአረንጓዴ አሻራ ትሩፋት
Feb 21, 2026 159
ደሴና ደብረ ማርቆስ፤ የካቲት 14/2018 (ኢዜአ)፡- ከተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ወደ ትርፍ ምርት-የአረንጓዴ አሻራ ትሩፋት በምስራቅ ሸዋ ዞን ከ119 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ዕቀባ ሥራ እየተከናወነ ነው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር ) ሀሳብ አመንጪነት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የአፈር ለምነትን በማሻሻል ምርታማነትን እያሳደገ መሆኑን አርሶ አደሮች ይመሰክራሉ። ባለፉት ዓመታት ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተከለቻቸው በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞች የአፈር ለምነትን በመመለስና የተፈጥሮ ሀብትን በመጠበቅ ረገድ ተጨባጭ ውጤት ማምጣታቸውን ከአርሶ አደሩ ባለፈ የተለያያዩ አለም አቀፍ ተቋማት ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል። በመርሃ-ግብሩ የተከናወኑ የአፈርና ውሃ እቀባ ሥራዎች ቀደም ሲል ተራቁቶ የነበረን መሬት እንዲያገግም አድርገዋል። ደርቀው የነበሩ ምንጮች እንዲፈልቁና የወንዞች የውሃ መጠን እንዲጨምር በማድረግም ለመስኖ ልማት ምቹ ሁኔታን ፈጥረዋል። ይህም በምርታማነት ላይ ከፍተኛ ለውጥ ያመጣ ሲሆን፣ በአንዳንድ አካባቢዎች በግማሽ ሄክታር መሬት ላይ ይገኝ የነበረውን 7 ኩንታል ምርት ወደ 20 ኩንታል አሳድጓል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የምስራቅ ጎጃምና የደቡብ ወሎ ዞን አርሶ አደሮችም በአረንጓዴ አሻራ የታገዘው የአፈርና ውሃ እቀባ ሥራ ምርታማነታቸውን በእጥፍ ማሳደጉን ይናገራሉ። በምስራቅ ጎጃም ዞን የደጀን ወረዳ የሽንቡሪ ቀበሌ አርሶ አደር በቃሉ ፈቃድ እንደሚሉት፣ ቀደም ሲል በእርሻ ማሳቸው ላይ ይገጥማቸው የነበረው የአፈር መሸርሸር ለምርታማነት መቀነስ ዋነኛ ምክንያት ነበር። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ያከናወኑት የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ የእርሻ ማሳቸውን ለምነት በከፍተኛ ደረጃ እንዲጨምር አድርጓል። ከ10 ዓመት በፊት በግማሽ ሄክታር መሬት ላይ ያገኙት የነበረው ምርት ከ7 ኩንታል በታች እንደነበር አስታውሰው፣ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በመታገዝ የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ በመስራታቸው አሁን ላይ ከ20 ኩንታል በላይ ምርት እንደሚያገኙ አመልክተዋል። ይህ ውጤት በዘንድሮው በጋ እየተካሄደ በሚገኘው የተፈጥሮ ሀብት ልማት ሥራ ላይ ያለማንም ቀስቃሽ በቁርጠኝነት ለመሳተፍ መነሳሳትን እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል። የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራው ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ ለውሃ ሀብት መጨመር ምክንያት ሆኗል። በምስራቅ ጎጃም ዞን የጎዛምን ወረዳ አርሶ አደር በእድሉ ጫኔ በበኩላቸው፣ ባለፉት ዓመታት ባከናወኗቸው የተፈጥሩ ሃብት ጥበቃ ሥራዎች የከርሰ ምድር ውሃ መጨመሩንና ደርቀው የነበሩ ምንጮች መፍለቃቸውን አመልክተዋል። ይህም ለመስኖ ልማት ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ስራ ላይ በመሰማራት ተጨማሪ ገቢ እንዳገኝ አድርጓል ብለዋል። በደቡብ ወሎ ዞን አርጎባ ብሔረሰብ ልዩ ወረዳም በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ተመሳሳይ ስኬቶች እየተመዘገቡ ነው። አርሶ አደር ሱለይማን መሀመድ እና ያስን መሀመድ እንደተናገሩት፣ በአረንጓዴ አሻራ የተሰሩ እርከኖችና ክትሮች የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ በማድረጋቸው በየሄክታሩ ከ2 እስከ 3 ኩንታል የምርት ጭማሪ አግኝተዋል። የወል መሬቶችን በማልማትም በቆላ ፍራፍሬና በእንስሳት እርባታ ዘርፍ ለአካባቢው ወጣቶች ሰፊ የስራ እድል መፈጠሩን አስረድተዋል። የምስራቅ ጎጃም ዞን የግብርና መምሪያ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ቡድን መሪ ንጉሴ ሽመልስ እንደገለጹት፣ በዘንድሮው በጋ ከአንድ ሺህ በላይ ተፋሰሶች ላይ 84 ሺህ ሄክታር መሬትን የሚሸፍን የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ ለማከናወን ታቅዶ እስካሁን ከ50 በመቶ በላይ ተከናውኗል። በተመሳሳይም የደቡብ ወሎ ዞን የግብርና መምሪያ ኃላፊ አህመድ ጋሎ፣ በዞኑ በ58 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሀብት ልማት ስራ ለማከናወን ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱንና እስካሁን ከ33 ሺህ ሄክታር በላይ መከናወኑን ገልጸዋል። አርሶ አደሩ በዘርፉ እያገኘ ያለው ተጨባጭ ጥቅም ለስራው ስኬታማነት ትልቁን ድርሻ እየተወጣ መሆኑንም አመልክተዋል።