አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ከ142 ሚሊዮን በላይ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Apr 13, 2026 78
ጎንደር፤ ሚያዚያ 5/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ከ142 ሚሊዮን በላይ ሀገር በቀል ችግኞች የማዘጋጀት ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ የመምሪያው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን አጠናክሮ በማስቀጠል የአካባቢውን ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው። ለዚህም በዞኑ ሥር ባሉ የተለያዩ ወረዳዎች በተቋቋሙ 12ሺህ የችግኝ ጣቢያዎች ከ142 ሚሊዮን በላይ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውና የአካባቢውን ስነ ምህዳር ለመጠበቅ የሚያግዙ ችግኞች እየፈሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ችግኞቹ በመጪው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የሚተከሉ መሆናቸውን ገልጸው፣ እስካሁን በተደረገ ጥረትም ቀድመው የሚፈሉ 76 ሚሊዮን ሀገር በቀል ችግኞችን በማፍላት የእንክብካቤ ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በክረምቱ ከሚተከሉ ችግኞች ውስጥ ከ40 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑት ኢኮኖሚያዊ ጥቅም የሚሰጡ አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ቡናና መሰል የፍራፍሬ ችግኞች እንደሆኑም አስረድተዋል። እንደ አቶ ንጉሴ ገለጻ፣ በመጪው ክረምት 33ሺህ ሄክታር የሚሸፍን የችግኝ ተከላ ሥራ ለማከናወን የቦታ መረጣና ሌሎች ዝግጅቶች እየተደረጉ ይገኛሉ።፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአካባቢን ስነ ምህዳር ከማስጠበቅ ባለፈ በርካታ ወጣቶች በግላቸው ችግኝ አፍልተው በመሸጥ የሥራ ዕድል እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንም አያይዘው ገልጸዋል። የዞኑ ህብረተሰብ ችግኝ የተተከለባቸውን ቦታዎች ከመከለል ባለፈ በራሱ ወጪ ሠራተኞችን ቀጥሮ የእንክብካቤና የጥበቃ ሥራ እያከናወነ መሆኑን ገልጸው፣ ባለፈው ዓመት ክረምት ከተተከሉ 121 ሚሊዮን በላይ ችግኞች 86 በመቶው ጸድቀዋል ብለዋል። የደን ልማት ሥራ ለግብርና ሥራችን መሰረት በመሆኑ በየዓመቱ በክረምት ወራት ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ ተሳትፎ እያደረጉ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የወገራ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር በላይነህ ስጦታው ናቸው፡፡ የጎንደር ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ ወጣት አምሳሉ ገነቱ በበኩሉ እንዳለው እሱና ጓደኞቹ በማህበር ተደራጅተው ባቋቋሙት የችግኝ ጣቢያ ሀገር በቀል የዛፍና የፍራፍሬ ችግኞችን አፍልተው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እየሆኑ መጥተዋል፡፡ ለመጪው ክረምትም ከ500 ሺህ በላይ ችግኞች በማፍላት ለገበያ ለማቅረብ እየተዘጋጁ መሆኑን ጠቁመው፣ ከችግኞቹ መካከል ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የአቮካዶ እና የማንጎ ዝርያዎች ይገኙበታል ብለዋል። የማዕከላዊ ጎንደር ዞን አሁናዊ የደን ሽፋን መጠን 15 ነጥብ 2 በመቶ መድረሱን ከዞኑ ግብርና መምሪያ የተገኘ መረጃ ያመለክታል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የፖለቲካ ቁርጠኝነትና የሕብረተሰብ ንቁ ተሳትፎ የታየበት በአፍሪካ ቀዳሚ ኢንሼቲቭ ነው
Apr 9, 2026 104
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡-የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የፖለቲካ ቁርጠኝነትና የህብረተሰብ ንቁ ተሳትፎ የታየበት በአፍሪካ ቀዳሚ ኢንሼቲቭ መሆኑን የብሄራዊ አረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ ሰብሳቢ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያ የምታስተናግደው 16ኛው የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አህጉራዊ ጉባኤ "ለሉዓላዊነት መተባበር" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን እየተካሄደ ነው። የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አባል ሀገራትና ታዛቢዎች እንዲሁም የዘርፉ ተዋንያን የሚሳተፉበት ጉባኤው በአፍሪካውያን መካከል ትብብርና አጋርነትን በመፍጠር አህጉራዊ የአደጋ ሥጋትን የመከላከልና የፋይናንስ አቅምን ማጠናከርን ያለመ ነው። ጉባኤው የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም፣ ለአደጋ ስጋት ምላሽ ለመስጠት እና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ አፍሪካ መር መፍትሔ ማፈላለግ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ምክክርና የጋራ መግባባት መፍጠር ያስችላል። የብሄራዊ አረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ ሰብሳቢ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) በመድረኩ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያስመዘገበችውን ስኬትና ለአፍሪካ ያላትን ተሞክሮ አቅርበዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የመጀመሪያ ምዕራፍ 50 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ስታቅድ በወቅቱ ምሁራን ሳይቀሩ ዕቅዱ ሊሳካ አይችልም የሚል ጥርጣሬ እንደነበራቸው አስታውሰዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እሳቤ መሆኑን ጠቅሰው፤ የተራቆተ መሬትን እንዲያገግም ማድረግ ሥነ-ምህዳሩን መመለስ እና ለግብርናና ከተማ ልማት ምቹ ከባቢ መፍጠር ነው ብለዋል። በዚህም የተለያዩ ሀገር በቀል እና ለተለያዩ አገልግሎት የሚውሉ ችግኞችን በመትከል የኢትዮጵያን ምድር አረንጓዴ ማልበስ መጀመሩን ገልጸዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከቀጣይነት ያለው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃን በማጠናከር የግብርና ሥራዎች ምቹ ሥነ-ምህዳር መፍጠሩን ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ የመላው ኢትዮጵያውያንና ተቋማት ትብብር የጋራ ውጤት ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ ከጠቅላይ ማኒስትሩ ጀምሮ የሁሉም አመራር ቁርጠኝነት የታየበት መሆኑን ጠቅሰው፤ ለጎረቤት ሀገራት ጭምር ተሞክሮ ሆኗል ብለዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ጭምር ተቀባይነት ማግኘቱን ገልፀው፣ ኬንያ በአስር ዓመት ውስጥ 15 ቢሊየን ችግኝ ለመትከል ተሞክሮ መውሰዷን ተናግረዋል።
ለአየር ንብረት ለውጥ የማትበገር አፍሪካን ለመገንባት አህጉራዊ አንድነታችን ወሳኝ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 9, 2026 214
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 1/2018 (ኢዜአ)፡- ለአየር ንብረት ለውጥ የማትበገር አፍሪካን ለመገንባት አህጉራዊ አንድነታችን ወሳኝ ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ዛሬ በሰው ልጅ መገኛዋ ኢትዮጵያ፣ በአፍሪካውያን መሰባሰቢያ አዲስ አበባ፣16ኛውን የአፍሪካ የሥጋት መከላከል ዐቅም ጉባኤ (ARC-COP16) በይፋ አስጀምረናል ብለዋል። አህጉራችን በአየር ንብረት ለውጥ ክፉኛ እየተፈተነች ትገኛለች ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፤ ሆኖም ይህ ፈተና ተስፋችንን የሚያጨልም፣ ጉዟችንን የሚገታ አይሆንም ሲሉም ገልጸዋል። በእልህ፣ በቁጭትና በእንችላለን ኅብረት አንድነታችንን የምናጠናክርበት አጋጣሚ ነው። እኛ አፍሪካውያን ከአደጋ በኋላ ለሚመጣ ርዳታ እጅ ከመዘርጋት ይልቅ፣ አደጋን ቀድሞ መከላከልና በሳይንሳዊ መንገድ ለመፍትሔ መዘጋጀት የህልውናችን መሠረት ሊሆን ይገባል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ በዚህ ረገድ ራዕይ ሰንቃ፣ ክንዷን አበርትታ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ዐቅም እየገነባች መሆኑን ገልጸው፤ በአረንጓዴ ዐሻራ የምድርን ገጽታ እየቀየርን መሆኑንም ተናግረዋል። በምግብ ሉዓላዊነት ንቅናቄ ራሳችንን ለመቻል እየተጋን ነው። በታዳሽ ኃይል ልማትም የአህጉራዊ ትሥሥር ገመድ እየሆንን ነው ብለዋል። ሰው ሠራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች በበዙበት፣ በአንጻሩ ዓለም አቀፋዊ ድጋፎች በቀነሱበት በዚህ ወቅት፣ የአፍሪካ ሥጋትን የመከላከል ዐቅም (African Risk Capacity-ARC) የመሰሉ አህጉራዊ ተቋሞቻችንን ማጠናከር አማራጭ የሌለው ጉዳይ መሆኑንም ገልጸዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው የአደጋ ሥጋትን በጥናት መለየት፣ ቀድሞ መከላከል፣ ችግር ሲከሠትም በአፍሪካዊ ዐቅም ምላሽ መስጠት ይገባል። ኢትዮጵያም ለዚህ የአፍሪካውያን ሌላኛው የሉዓላዊነት ግብ መሳካት በአርአያነት ትተጋለች ብለዋል።
የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራና የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራዎች የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ለአፍሪካ ምሳሌ ናቸው
Apr 8, 2026 554
አዲስ አበባ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ፣ በኮሪደርና በወንዝ ዳርቻ ልማት የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከልና ምላሽ ለአፍሪካውያን ምሳሌ የሆኑ ተግባራትን እያከናወነች እንደምትገኝ የኢትዮጵያ አደጋ ሥጋት አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት 16ኛው የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አህጉራዊ ጉባኤ "ለሉዓላዊነት መተባበር" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን እየተካሄደ ነው። 39 የአፍሪካ አደጋ ሥጋት አቅም አባል ሀገራትና ሌሎች የዘርፉ ተዋንያን እየተሳተፉበት የሚገኘው ይህ ጉባኤ፤ በአፍሪካውያን መካከል ትብብርና አጋርነትን በመፍጠር አህጉራዊ የአደጋ ሥጋትን የመከላከልና የፋይናንስ አቅምን ማጠናከርን ያለመ ነው። የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ አፍሪካውያን የምግብ ሉዓላዊነትን በራሳቸው አቅም ለማረጋገጥ ለጋራ ግብ የሚተባበሩበት ወሳኝ ወቅት ላይ ናቸው፡፡ የአፍሪካ የአደጋ ሥጋት አቅም አህጉራዊ የምግብ ሉዓላዊነትን በራስ አቅም ለማሳካት ጥረት እያደረገ መሆኑን ገልጸው፤ የተቀናጀ የአደጋ ሥጋት ምላሽ መስጠት የሚያስችል አህጉራዊ የፋይናንስ አቅም መገንባት ይገባል ብለዋል፡፡ የአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 ግቦችን በማሳካት የምንመኛትን አፍሪካ ለመገንባት የሀገራት ጠንካራ የፖለቲካ ቁርጠኝነትና ቀጣይነት ያለው የፋይናንስ ስርዓት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ቀዳሚ አጀንዳ መደረጉን ገልጸው፤ ጠንካራ ተቋማዊ አደረጃጀት በመፍጠር የተሟላ ድጋፍ ማድረግ የሚያስችል አቅም ተገንብቷል ብለዋል፡፡ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ አረንጓዴ አሻራ፣ መስኖ፣ የሌማት ትሩፋት፣ የታዳሽ ኃይል እና ሌሎችም ኢንሼቲቮች የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን በመከላከል እንዲሁም የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን በመመከት፣ የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥና የአደጋ ምላሽ በመስጠት ለአፍሪካና ለዓለም ምሳሌ እየሆነች ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማትና ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር ኢኮኖሚ በመገንባት ያሳየችው ስኬት ጉባኤውን ለማስተናገድ ተመራጭ እንዳደረጋትም ኮሚሽነሩ አንስተዋል። የአፍሪካ አደጋ ስጋት አቅም ጉባኤ ኢትዮጵያ ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም በማሟላትና የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ያስመዘገበቻቸውን ተሞክሮዎች የምታጋራበት መድረክ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ሥርዓት ለመገንባት የተገበረቻቸው ኢኒሼቲቮች የምግብ ሉዓላዊነትን እና የሰብዓዊ ድጋፍ ሉዓላዊነትን ማሳካት እንደሚያስችሉ ተናግረዋል፡፡ በአዲስ አበባ የሚሰሩ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራዎች የአየር ንብረት ለውጥን መከላከልና የአደጋ ምላሽ በመስጠት ለአፍሪካውያን ምሳሌ የሆኑ የተግባር ማሳያዎች ናቸው ብለዋል፡፡
ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቃሜታ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Apr 8, 2026 193
አሶሳ፤መጋቢት 30/2018 (ኢዜአ)፦ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቃሜታ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ በክልሉ ዑራ ወረዳ የችግኝ ጣቢያዎች በመገኘት ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የችግኝ ዝግጅትን ተዘዋውረው ተመልክተዋል። ከጉብኝቱ በኋላ ባደረጉት ንግግርም በክልሉ ብሎም እንደ ሀገር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። የልማት ስራው ዘንድሮም ልዩ ትኩረት የተሰጠው መሆኑን አንስተው ለዚህም በክልሉ በቂ የችግኝ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቃሜታ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን በጉብኝታችን አረጋግጠናል ብለዋል። ከዚህ ፊት የተተከሉ ችግኞች ያሉበትን ደረጃ እና በወረዳው በአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎችንም ርእሰ መስተዳድሩ ተዘዋውረው ተመልክተዋል።
ኢትዮጵያ ከካርበን ግብይት መስፈርቶች ጋር የሚጣጣሙ የደን አያያዝ ስራዎችን እያከናወነች ነው
Apr 4, 2026 219
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፍ የካርበን ግብይት መስፈርቶች ጋር የሚጣጣሙ ዘላቂ የመሬትና የደን አስተዳደር ልምዶችን እያሳደገች መሆኑን የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ገለጹ። ዶክተር አደፍርስ ወርቁ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የካርበን ክምችት መኖሩን በማንሳት፤ አብላጫው በደን ሀብት ውስጥ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የደን ሽፋንን ከማሳደግ ባለፈ ሀገሪቱ ከካርበን ሽያጭ የምታገኘው ገቢ እንዲጨምር የጎላ ሚና እየተጫዎተ እንዳለ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በርካታ የብዝሃ ህይወት ባለቤት በመሆኗ የተሻለ የካርበን ክምችት ለመያዝ የሚያስችል ተስማሚ ሥነ-ምህዳር እንዳላት ዶክተር አደፍርስ ገልጸዋል። ሀገሪቱ በአየር ንብረትና በአካባቢ ጥበቃ ስራዎች ላይ በንቃት እየተሳተፈች መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም ካርበንን ከአየር ላይ በማስወገድ በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ መንገድ እንዲከማች እያደረገ ነው ብለዋል። ቀደም ሲል በደን መመንጠርና ባልተገባ የመሬት አያያዝ ምክንያት ወደ ህዋ ይለቀቅ የነበረውን ሙቀት አማቂ ጋዝ መከላከል የሚያስችሉ ተግባራት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አማካይነት እየተተገበሩ እንዳለ አስረድተዋል። በዚህም ከካርበን ግብይት መስፈርቶች ጋር የሚጣጣሙ ዘላቂ የመሬት እና የደን አሥተዳደር ልምዶችን ማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙም ገልጸዋል። ሁለተኛው ደግሞ እጽዋት በሚተከሉበት ወቅት ቀደም ሲል ወደ ህዋ የሄደውን ካርበን አምቀው የሚመልሱበትን አሰራር ተግባራዊ በማድረግ እና ከልቀት የተጠበቀውን ካርበን ገበያ ለማቅረብ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ እያከናወነች ባለችው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አማካኝነት የካርበን ሽያጭን ለማጠናከር እየተሰራ መሆኑንና ሀገራት ከኢትዮጵያ ጋር የግዢ ውል ስምምነት እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም የኖርዌይ መንግስት እንደመነሻ የ75 ሚሊዮን ዶላር የካርበን ግዢ እንዲሁም የዓለም ባንክም እንዲሁ የግዢ ውል ማሰሩን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ኖርዌይ እና የዓለም ባንክ ሊገዙት ከሚፈልጉት በላይ ካርበን ማመንጨቷን ጠቁመው፤ እስከ አንድ ቢሊየን ዶላር ሊያመጣ የሚችል ካርበን ሀብት መኖሩን ገልጸዋል። በዓለም ገበያ ላይ ለካርበን ግዢ የሚመደበውን ከፍተኛ ሀብት ወደ ኢትዮጵያ የካርበን ሽያጭ ማምጣት የሚያስችሉ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙም ጠቁመዋል። በዓለም ላይ ያለውን የካርበን ፋይናንስ ወደ ኢትዮጵያ ለማምጣት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ከማጠናከር ባለፈ ሰነዶች የማደራጀትና ሌሎች ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አስታውቀዋል።
ኢትዮ ቴሌኮም ለዲጂታልና ታዳሽ ሃይል ልማት በልዩ ትኩረት እየሰራ ነው
Apr 3, 2026 454
አዳማ ፤መጋቢት 25/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮ ቴሌኮም ዘመናዊ የቴሌኮም አገልግሎትን ከማስፋት ባሻገር ለዲጂታልና የታዳሽ ሃይል ልማት በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን የኩባንያው ዋና ስራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ። ኢትዮ ቴሌኮም በአዳማ ከተማ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ ማዕከል በመገንባት በዛሬው እለት አገልግሎት አስጀምሯል። በመርሃ ግብሩ ላይ በመገኘት ንግግር ያደረጉት የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ፤ በኢትዮጵያ የዲጂታልና የታዳሽ ሃይል ልማት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በአዳማ ከተማ ተገንብቶ በዛሬው እለት ለአገልግሎት ክፍት የተደረገው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ ማዕከልም የዚሁ ልማት ጥረት አካል መሆኑን ጠቁመዋል። የአዳማው ማእከል በአንድ ጊዜ 12 ተሽከርካሪዎችን ቻርጅ የሚያደርግ አቅም እንዳለው ተናግረው በሌሎች አካባቢዎችም የማስፋት እቅድ መኖሩን ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮም ከፈጣንና ዘመናዊ የቴሌኮም አገልግሎት በተጨማሪ ለዲጂታልና የታዳሽ ሃይል ልማት በልዩ ትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በዚህም መሰረት አዲስ አበባን ጨምሮ በክልል ከተሞች የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጀ ማድረጊያ ማዕከላትን በማስፋፋት ላይ መሆኑን ገልጸዋል። የአዳማ ከተማ ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ፤ የስማርት አዳማ ፕሮጀክት ተቀርፆ አሰራርና አገልግሎቶችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማስደገፍ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህ ሂደት የኢትዮ ቴሌኮም አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን አንስተው በከተማዋ ተገንብቶ ለአገልግሎት የበቃው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ ማድረጊያ ማዕከል ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው አንስተዋል።
በመጪው ሚያዚያ ወር በአብዛኞቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የኢትዮጵያ አካባቢዎች የተሻለ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ ይኖራል
Apr 3, 2026 149
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 25/2018(ኢዜአ)፦ በመጪው ሚያዚያ ወር በአብዛኞቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በመጠንና ሥርጭት የተሻለ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ እንደሚኖር የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፤ ከመጋቢት 23 እስከ ሚያዚያ 22/2018 ዓ.ም የበልግ ዝናብ በመጠንና ስርጭት ከፍተኛ ድርሻ የሚወስድበት ወቅት መሆኑን ገልጿል። በዚህም በመጪው ሚያዚያ ወር በአብዛኛዎቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ከቀደሙት ሁለት የበልግ ወራት በመጠንና ሥርጭት የተሻለ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ እንደሚኖር አስታውቋል። ይህም የአየር ጠባይ ሁኔታ የበልግ አብቃይና ተጠቃሚ አካባቢዎች ለሚያከናውኑት የግብርና ሥራ አመቺ ሁኔታን እንደሚፈጥር ይጠበቃል ብሏል ኢንስቲትዩቱ በመግለጫው። በተለይም በተያዘው የመጋቢት ወር የሚስተዋለው ተከታታይ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ በቡቃያና በተለያየ የዕድገት ደረጃ ላይ ለሚገኙ የበልግ ሰብሎች ምርታማነት ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጿል። በደቡብና ደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያ የሚጠበቀው እርጥበታማ የአየር ሁኔታ ለቦረና፣ ጉጂና መሰል ከፊል አርብቶ አደር አካባቢዎች ሰብል ልማት፣ ግጦሽ መሬትና የውሃ አቅርቦት ወሳኝ መሆኑንም አመላክቷል። በዚህም የበልግ አብቃይ አካባቢ አርሶና አርብቶ አደሮች ማሳቸውን በማዘጋጀት የሚጠበቀውን አመቺ እርጥበታማ የአየር ሁኔታ ለመጠቀም ዝግጅት ማድረግ እንደሚያስፈልግ አሳስቧል። በበልግ ዝናብ መዋዠቅ አዝማሚያ ምክንያት ዝናብ አጠር የሆኑ አካባቢዎች የሚያጋጥማቸውን ተከታታይ ደረቃማ ሁኔታ ለመቋቋም እርጥበትን በማሳ ማቆየት የሚያስችል ስራ ማከናወን እንደሚገባቸውም ኢንስቲትዩቱ አስውገንዝቧል። በሌላ በኩል በአንዳንድ አካባቢዎች በሚኖር ከባድ ዝናብ ሊፈጠር ከሚችል የመሬት መንሸራተት፣ የአፈር መሸርሸርና ቅፅበታዊ የጎርፍ አደጋ ተጋላጭነት ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ አሳስቧል።
የክልሉ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የዜጎችን ተጠቃሚነት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ነው
Apr 3, 2026 152
ባህር ዳር፤ መጋቢት 25/2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በለውጡ ዓመታት የተተገበረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የዜጎችን ተጠቃሚነት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከእለት ወደ እለት ስኬታማ እየሆነ መምጣቱ እየተመሰከረለት ነው። በመርሃ ግብሩ በብዛትና እና በአይነት መጠነ ሰፊ ችግኞች ተከላ መካሄዱን ለአካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም፤ ለደን ሽፋን መጨመር ብሎም የምግብ ዋስትን ለማረጋገጥ እያስቻለ ነው። የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ መሰሉ ብርሃኑ ለኢዜአ እንዳሉት፤በለውጡ ዓመታት የተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የዘርፉን ልማት ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ነው። መርሃ ግብሩ ለአካባቢ ጥበቃና ለአየር ንብረት ለውጥ መሻሻል፤ ለደን ሽፋን መጨመር እና የምግብ ዋስትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማበርከት ላይ መሆኑንም አስረድተዋል። መርሃ ግብሩ ተግባራዊ መደረጉ በክልሉ 13 ነጥብ 9 በመቶ የነበረውን የደን ሽፋን ወደ 18 ነጥብ 9 በመቶ ለማስደግ እንደተቻለም ነው የተናገሩት። በነዚሁ የለውጥ አመታት በ22 ሺህ 189 ተፋሰሶች ላይ በተካሔደው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ምርታማነት ለማሳደግ ያስቻለ መሆኑንም አብራርተዋል። የአረንጓደ ልማቱ በተለይም ለንብ ማነብ፣ ለእንስሳት እርባታና ለፍራፍሬ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አንስተዋል።
በአዲስ አበባ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ ተጠናክሮ ቀጥሏል
Apr 2, 2026 167
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ሀገር በቀል እና ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራው ተጠናክሮ መቀጠሉ ተገለጸ፡፡ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እና ዘላቂ የአካባቢ ጥበቃን ለማረጋገጥ፣ የለውጡ መንግስት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን በፖሊሲ ደረጃ ቀርጾ ተግባራዊ በማድረጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ነው፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን በመትከል ግቡን እውን ማድረግ ችሏል፡፡ በ2018 ዓ.ም ይህንን ሀገራዊ ስኬት ቀጣይነት ባለው መልኩ ለማከናወን በሀገር አቀፍ ደረጃ 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ ወደ ስራ ተገብቷል። ይህንን ግብ ማሳካት የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች አዲስ አበባን ጨምሮ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በስፋት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በየካ ክፍለ ከተማ የከተማ ውበት እና አረንጓዴ ልማት ጽህፈት ቤት የግብአት አቅርቦትና የችግኝ ጣቢያ ባለሙያ የሆኑት ስንታየሁ ግርማ፤ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ በስፋት እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። በፈረንሳይ የሃ የችግኝ ጣቢያ ለዘንድሮው የክረምት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚውሉ 150ሺህ የሚሆኑ ሀገር በቀል፣ የውበትና የፍራፍሬ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡ እየተዘጋጁ ካሉ የሀገር በቀል የእጽዋት ዝርያዎች መካከል ወይራ እና ብርብራ ተጠቃሽ ሲሆኑ፤ ከፍራፍሬ ዝርያዎች ደግሞ ካዝሚር እና አቮካዶ በስፋት እየተዘጋጁ እንደሚገኙ አብራርተዋል። ይህ የችግኝ ዝግጅት ስራ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የሚደረገውን ጥረት ከመደገፍ ባለፈ፣ ለምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥ የሚውሉ የፍራፍሬ ዝርያዎችን በማካተት ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በጣቢያው ለዘንድሮ አረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ለተከላ የሚሆኑ የፍራፍሬና ሀገር በቀል ችግኞችን ጨምሮ ሌሎች ዝርያ ያላቸው ችግኞች እያዘጋጁ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የሶስኒ ችግኝ ጣቢያ አስተባባሪ አበበች መካ ናቸው። በዚህም በጣቢያው ከ1 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ ችግኞች ለማዘጋጀት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው ችግኞች ፍሬያማ እንዲሆኑ ጣቢያው ለችግኞች ተገቢውን እንክብካቤ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማ ውበት እና አረንጓዴ ልማት ቢሮ የአረንጓዴ ቦታዎች አያያዝ፣ ክትትልና ቁጥጥር ዳይሬክተር ሲሳይ አጥናፉ፤ ለዘንድሮው የክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስድስት ሚሊየን ችግኞችን ለማዘጋጀት ታቅዶ በስፋት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በመዲናዋ በሚገኙ የችግኝ ጣቢያዎች ለተከላው የሚያስፈልጉ የሀገር በቀል እና የፍራፍሬ ችግኞች በልዩ ትኩረት በማዘጋጀት ላይ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋገረ እና ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለች ሀገርን ለማስተላለፍ የሚያስችል መሠረት የጣለ ታላቅ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው።
የኢትዮጵያ የከተማና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት ስኬቶች በአርዓያነት የሚወሰዱ ናቸው
Apr 2, 2026 186
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ የከተማና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ የልማት ስኬቶች የተሻለች አፍሪካን ለመገንባት በአርዓያነት የሚወሰዱ መሆናቸውን የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ጋዜጠኞች ገለጹ። የኢትዮጵያ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ስኬቶች በሀገር ገጽታ በመገንባት የከተማ ነዋሪዎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማሻሻል አስተማማኝ ምኅዳር ፈጥረዋል። በአዲስ አበባ ተጀምሮ በበርካታ ከተሞች ተግባራዊ የተደረገው የኮሪደር ልማትም የንግድና ቱሪዝም እንቅስቃሴን በማሳለጥ ዘመናዊ፣ ውብና ፅዱ ከተሞችን እየፈጠረ ይገኛል። በሌላ መልኩም ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዕድገት ዘላቂነትን ለማረጋገጥ ተግባራዊ ያደረገችው የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ የልማት አቅጣጫም ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው። የአረንጓዴ አሻራና የታዳሽ ኃይል፣ የበጋና የመኸር ወቅት የሰብል ምርታማነት፣ ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄና የአካባቢ ጥበቃ የልማት መርሃ ግብሮች ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ግንባታ አብነቶች ናቸው። በተለይም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ኢትዮጵያን የአፍሪካ ሳንባ የማድረግ ትልም ያስመዘገበው ስኬት የተራቆቱ አካባቢዎችን በደን በመሸፈን ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ ይገኛል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታም አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅና እየተቸረው የሚገኝ አስደናቂ የልማት ትልም ሆኗል። የደቡብ ሱዳን፣ ዑጋንዳና ቡሩንዲ ጋዜጠኞች ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ በከተማ ልማትና በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም አስደናቂ የልማት ጉዞ ላይ መሆኗን መስክረዋል። የደቡብ ሱዳን ጋዜጠኛ አይዛክ ዱዶሩ አማኑኤል፤ ለሁለተኛ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ በመጣበት አጋጣሚ አዲስ አበባ የሚታይና የሚጨበጥ የልማት እንቅስቃሴ ያላት ከተማ መሆኗን መገንዘቡን ገልጿል። ይህም በኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ ፈጣንና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኢኮኖሚ ዕድገትን የሚያፋጥኑ የልማት መርሃ ግብሮች እየተገነቡ እንደሚገኝ ማሳያ ነው ብሏል። የቡሩንዲ ጋዜጠኛው ሜሻ ኬንዲ ኩምንጋም የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ የልማት መርሃ ግብሮች የተሻለች አፍሪካን ለመገንባት ትምህርት የሚቀሰምበትና አስደናቂ የአመራር ቁርጠኝነት ውጤት መሆኑን ተናግሯል። የዑጋንዳ ጋዜጠኛ ኮሙ ዴኒስ በበኩሉ፤ የአዲስ አበባ ከተማ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ የልማት መርሃ ግብሮች ጥራትን ከውበት ያሰናሰሉ አስደናቂ የልማት ውጤቶች መሆናቸውን ገልጿል። የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የታዳሽ ኃይል ልማት መርሃ ግብሮች ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው ዓለም አቀፍ የልማት ውጤቶች እንደሆኑ ተናግሯል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኢኮኖሚ ግንባታም የተሳለጠ ዕድገት የሰፈነባት አፍሪካን እውን ለማድረግ በተሞክሮነት የሚወሰድ መሆኑን አንስቷል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም የአካባቢ መራቆትን በደን በመሸፈን የተፈጥሮ ሚዛንን የሚያስጠብቅ ወሳኝ የልማት እርምጃ መሆኑን አብራርቷል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ረገድ ዘርፈ ብዙ ፋይዳዎችን እያበረከተ ነው
Apr 2, 2026 157
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018(ኢዜአ)፦በሀገራዊ የለውጥ ዓመታት ተግባራዊ የተደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የአፈር ለምነትን በማሳደግና ምርትና ምርታማነትን በማረጋገጥ ረገድ ዘርፈ ብዙ ፋይዳዎችን እያበረከተ መሆኑን የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ ገለፀ። መጋቢት 24 ቀን 2010 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ፖለቲካዊ ታሪክ ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የተከፈተበትና ሀገራዊ ለውጡ እውን የሆነበት ዕለት ነው፡፡ ይህንኑ ለውጥ ወደ ተግባር ከቀየሩትና የለውጡ ትሩፋት ተብለው ከሚጠቀሱ ስኬቶች መካከል ደግሞ የአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄ በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም. የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር፣ ባለፉት ስድስት ዓመታት የኢትዮጵያን የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ የመቋቋም አቅም ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ትልቅ ሀገራዊ ንቅናቄ ነው። የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ዋና ግቡ የሀገሪቱን የደን ሽፋን ማሳደግ፣ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ እና ለቀጣዩ ትውልድ ምቹ አካባቢን መፍጠር መሆኑ ይታወቃል፡፡ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች የተተከሉ ሲሆን የኢትዮጵያን የደን ሽፋን ከ23 ነጥብ 6 በመቶ በላይ ማድረስ ማስቻሉ ከንቅናቄው ስኬቶች መካከል ተጠቃሽ ነው፡፡ የአረንጓዴ አሻራ ሰፊ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታዎች እያስገኘ ሲሆን የምግብ ሉዓላዊነትን ከማረጋገጥ፣ ከሥራ ዕድል ፈጠራ እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ አድናቆትን ከማስገኘቱም በላይ፣ ለጎረቤት ሀገራትም ችግኞችን በማካፈል ቀጠናዊ ትስስርን ማጠናከር አስችሏል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ መንግስት ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሰጠው ትኩረትም የተፈጥሮ ሃብቶችን በማስጠበቅ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማበርከት ያስቻለ ውጤት ተገኝቷል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል እየተገበረችው ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የአካባቢ ስነ-ምህዳርን በመጠበቅና የደን ሽፋንን በማሳደግ በኩል ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በዚህም በቅርቡ በተለያዩ የአገሪቷ ክፍሎች በተደረገ ጥናት እስካሁን ከተተከለው 48 ቢሊዮን ችግኝ 30 በመቶ የሚሆነውን በአባይ ተፋሰስ የሚገኙ ወረዳዎች ላይ መተከሉን ያሳያል ነው ያሉት። እንዲሁም በአዋሽ ተፋሰስ እና ስምጥ ሸለቆ ውስጥም ተመሳሳይ ጥናት መካሄዱን ገልፀው፤ የመሬቱ የደን ሽፋን በማደጉ የከርሰ ምድር ውሃው በከፍተኛ ሁኔታ መጨመር መቻሉን ጥናቱ ያመለክታል ብለዋል። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት እና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ፋኖስ መኮንን በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን የደን ሽፋን በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። መርሃ ግብሩ ከተጀመረበት ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በተተከለው ችግኝ ተመናምኖ የነበረው የደን ሽፋን ከጊዜ ወደ ጊዜ እንዲሻሻል አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። በዚህም አሁን ላይ የደን ሽፋኑን ከ17 ነጥብ 2 በመቶ ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ማድረግ መቻሉን ባለፈው ዓመት የተደረገ ጥናት እንደሚያሳይም ጠቅሰዋል። መርሀ-ግብሩ በኢትዮጵያ ያለውን የደን ሽፋን በእጅጉ ከማሳደጉ ባሻገር በአትክልትና ፍራፍሬ ምርትና ምርታማነት በመጨመር ከህዝቡ ተጠቃሚነት ባሻገር ወደ ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሪ እያስገኘ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት በምርምር ማገዝ ይገባል
Mar 31, 2026 189
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የምታደርገውን ጥረት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በምርምርና በሳይንስ ማገዝ እንዳለባቸው የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለፁ። የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎች የአየር ንብረት ትግበራ ፎረም የመጀመሪያ ጠቅላላ ጉባኤ እየተካሄደ ነው። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት፤ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በሚደረገው ብሔራዊ ጥረት ሊኖራቸው የሚገባውን ስትራቴጂያዊ ሚና አፅንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። ሳይንሳዊ የመፍትሄ ሃሳቦችን በማፍለቅ በኩል በቅንጅት መስራት እንደሚጠበቅባቸውም አቶ ስዩም አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመመከት በአየር ንብረት የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂን በመተግበር ቀዳሚ መሆኗን ጠቁመዋል። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን መትከል እና በታዳሽ ኃይል ልማት የተመዘገቡት ስኬቶች ኢትዮጵያ ለአፍሪካና ለዓለም አርአያ መሆኗን የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል። ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጥናትና ምርምር ስራዎቻቸው፣ የድህረ-ምረቃ ተማሪዎች የመመረቂያ ጽሁፎችንና ጆርናሎቻቸውን በአየር ንብረት ለውጥና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ መሆን አለባቸው ብለዋል። ፎረሙ የፖሊሲ አውጪውንና የትምህርት ተቋማቱን የተቀናጀ ስራ የሚያጠናክር መድረክ እንደሆነም ጨምረው ገልጸዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአየር ንብረት ጉዳዮችን በበላይነት እንደሚመራ ተቋም ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር የጀመረውን ቅንጅት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ክፍሌ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲዎች የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ ሳይንሳዊ መፍትሄዎችን በማፍለቅ በኩል ከፍተኛ ሚና አላቸው። እንደሀገር እየተተገበረ ባለው የአረንጓዴ አሻራ ልማት እና የአየር ንብረት መቋቋም አቅም ግንባታ ስራዎች ላይ የዩኒቨርሲቲዎች ተሳትፎ ከንድፈ ሀሳብ ወደ ተግባር የተሻገረ መሆን እንዳለበትም ተናግረዋል። የፎረሙ መመስረት ለአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄ ፍለጋ ትልቅ ምዕራፍ መሆኑን ገልጸው እንደሀገር የተጀመሩ ሥራዎችን መደገፍ የሚያስችል ነው ብለዋል።
በዞኑ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ ለመስኖ ልማት መስፋፋት አመቺ ሁኔታን ፈጥሯል
Mar 30, 2026 182
ጎንደር መጋቢት 21/2018 (ኢዜአ) :-በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተካሄደው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት ስራ የከርሰ ምድር ውሃ አቅርቦትን በማሻሻል ለበጋ መስኖ ልማት መስፋፋት አመቺ ሁኔታ መፍጠሩን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ በአማራ ክልል የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራው ከ2003 ዓ/ም ጀምሮ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ይገልፃል። የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃውም የአፈር ክለትን በመቀነስ ውሃማ አካላትና የመስኖ መሰረተ ልማት በደለል እንዳይሞሉ በማድረግ የሰብል፣ የእንስሳትና ፍራፍሬ ምርታማነትን ለማሳደግ አስተዋፅኦ እያደረገ ይገኛል። የመምሪያው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ ለኢዜአ እንደገለጹት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተከናወነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት የለም አፈር መከላትን በማስቀረት ለሰብል ምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። ይህም የከርሰና ገጸ ምድር ውሃ አቅም እንዲጨምር በማድረግ አርሶ አደሩ በዓመት እስከ ሶስት ጊዜ በመስኖ በማምረት የምግብ ሉዓላዊነቱን ለማረጋገጥ እየረዳው መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ ከአምስት ሄክታር በታች የነበረውን ዓመታዊ የመስኖ ልማት ስራ አሁን ላይ ወደ 40 ሺህ ሄክታር መሬት በመስኖ እንዲለማ የሚያስችል ውጤት ማስገኘቱን አስረድተዋል፡፡ በዞኑ ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተጠብቀው እየለሙ የሚገኙ ተፋሰሶች ቁጥር 955 መድረሱን ጠቁመው ይህም የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብሩ እንዲሳካ ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ብለዋል። አሁን ላይ በንብ ማነብ፣ በእንስሳት ማድለብና በወተት ላሞች እርባታ ለተሰማሩ 1 ሺህ 350 ወጣቶች የስራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማስቻሉን ተናግረዋል፡፡ በዘንድሮ በጋም በድግግሞሽ ከ11 ሚሊዮን በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች ባካሄዱት የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ 57 ሺህ 370 ሄክታር የተራቆተ መሬት ላይ የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ማከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ የጎንደር ዙሪያ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር ሰጠኝ አለነ እንደገለጹት በበጋው የምናከናውነው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት ስራ በመስኖ፣ በእንስሳትና በሰብል ልማት ምርታማነታቸው እንዲያድግ አስችሏል። በበጋ መስኖ በመታገዝ በአንድ ሄክታር መሬታቸው ላይ ቲማቲም፣ ሽንኩርትና ጥቅል ጎመን አምርተው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ያስቻላቸው መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የጭልጋ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር እሱባለው መሳፍንት በበኩላቸው በለሙ ተፋሰሶች ላይ በ15 ዘመናዊ የንብ ቀፎዎች ታግዘው ማር አምርተው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የህልውናችን መሰረት መሆኑን በመገንዘባችን በልማት ቡድኖች ተደራጅተን በየዓመቱ በግልና በወል መሬቶች ላይ የእርከንና ክትር ስራዎችን እያከናወንን እንገኛለን ብለዋል፡፡
የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ የብዝኃ ሕይወት ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውል ያስችላል
Mar 29, 2026 308
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፡- የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ኢትዮጵያ ያላትን ዕምቅ የብዝኃ ሕይወት ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል ገንቢ ሚና እንዳለው የዘርፉ ምሁራን ገለጹ፡፡ በአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የአካባቢ ሕጎችና ደረጃዎች ዴስክ ኃላፊ ወንደሰን ታደሰ፤ ኢትዮጵያ የውኃ፣ የደን፣ የዓየር ንብረት አገልግሎት፣ የቁጥጥርና ቱሪዝም ሥርዓተ-ምኅዳር ብትታደልም በሚገባት ልክ አልተጠቀመችም ብለዋል። የሥርዓተ-ምኅዳር ጉዳዮች በሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ ጉዳዮች በከፍተኛ ጫና ላይ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ በአገልግሎቱ አቅራቢዎችና ተጠቃሚዎች መካከል የጋራ መግባባትን በመፍጠር ዘላቂ የአካባቢ ጥበቃ ሥርዓትን ማጠናከር እንደሚያስችልም አስረድተዋል። የፋርም አፍሪካ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ሸዊት አማኑኤል በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያን የብዝኃ ሕይወት ሃብቶች ለሕብረተሰቡ ይበልጥ ጥቅም ላይ እንዲውሉ የሚያስችል ሥራ እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ የባሌ አካባቢ ማኅበረሰብ ተፈጥሮን በመንከባከብ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ተጠቃሚ መሆን መጀመሩን ገልጸው፤ ይህ በሁሉም አካባቢዎች መስፋት እንዳለበት አመላክተዋል። መንግሥት በአረንጓዴ ዐሻራና በአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ማስመዝገቡን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ ያላትን የብዝኃ ሕይወት ሀብት ይበልጥ መለየትና ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ በመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የውኃ ሀብትና ሀይድሮሎጂ መምህር ዓለምአየሁ አባተ (ዶ/ር)፤ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ማኅበረሰቡ የሠራበትን እንዲያገኝ በማድረግ የተጠናከረ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ማከናወን ያስችላል ብለዋል፡፡ በባሌ ኢኮሎጂ በ20 ወረዳዎች በመሰማራት እየሠሩ መሆኑን የገለጹት የፋርም አፍሪካ ፕሮግራም ሥራ አስኪያጅ ፈይሳ አሰፋ፤ በኢትዮጵያ የካርበን ክፍያ መጀመሩ የሕብረተሰቡን የአካባቢ ጥበቃ ተነሳሽነት ያሳድጋል ብለዋል፡፡ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጁ ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የብዝኃ ሕይወት ሀብት ጠብቃ እንድትቆይና ማኅበረሰቡ ተገቢውን ጥቅም እንዲያገኝ ያስችላል ሲሉም አስገንዝበዋል።
በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ ነው
Mar 28, 2026 200
አምቦ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በጽህፈት ቤት የደን ልማት ባለሙያ ጉደታ ጡሪ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ እየተዘጋጁ ከሚገኙ ችግኞች መካከል ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ዝርያዎች እንደሚገኙበት ተናግረዋል። በክረምቱ ወራት አጠቃላይ ከ94 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የችግኝ ተከላ እንደሚከናወን ገልጸው፤ የችግኝ ማፍላት ስራው በዞኑ በሚገኙ ሁሉም ወረዳዎች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ባሳተፈ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ዝግጅቱ የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንዲቻል ምርታማነታቸው ከፍተኛ በሆኑና በተሻሻሉ የችግኝ ዝርያዎች ላይ ትኩረት ማድረጉንም ጠቅሰዋል። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሮች አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተው፤ ችግኞችን የመንከባከብና የመጠበቅ ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑንም አክለዋል። የተተከሉ ችግኞች የአካባቢ ስነ-ምህዳርን ከመቀየር አንጻር ከፍተኛ ሚና ከመጫወታቸው ባለፈ፣ ደርቀው የነበሩ ኩሬዎች ዳግም ውሃ እንዲይዙ በማድረግ ለአርሶ አደሩ ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል ነው ያሉት። ባለፉት ሰባት ዓመታት በድምሩ 616 ሺህ 613 ሄክታር መሬት ላይ ችግኞች መተከላቸውን አስታውሰው፤ የአካባቢው ማህበረሰብ ያለውን ደን የመጠበቅ ባህላዊ እሴት ለአረንጓዴ ልማት ስራው ስኬታማነት ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን ገልጸዋል።
ለቀጣዩ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ ነው
Mar 27, 2026 183
ሆሳዕና፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ ሻራ መርሐ-ግብር የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ደንና አካባቢ ጥበቃ ልማት ቢሮ አስታውቋል። የቢሮው ኃላፊ አብርሃም መጫ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ባለፉት 7 ዓመታት በክልሉ 450 ሺህ ሔክታር በአካባቢ ጥበቃና በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ማልማት ተችሏል። በዚህም የአፈር ለምነትን በማስጠበቅ፣ የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥን ጨምሮ በበርካታ ዘርፎች ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን አብራርተዋል። በዚህ ዓመትም 270 ሚሊየን የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች በመትከል 80 ሺህ ሔክታር መሬትን ለማልማት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሠራን ነው ብለዋል። ሥነ-ምኅዳርን መሠረት ያደረጉ ለምግብነትና ለሌሎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የሚውሉ ችግኞችን የማፍላትና የማዘጋጀቱ ተግባር እየተከናወነ እንደሚገኝም ነው ያረጋገጡት።
የበልግ ዝናብ ስርጭት ለግብርና ምርታማነትና ለእንስሳት መኖ አቅርቦት ከፍተኛ ፋይዳ ያለው ነው-የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት
Mar 26, 2026 290
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018(ኢዜአ)፦የዘንድሮው የበልግ ዝናብ ስርጭት በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ለሚከናወኑ የግብርና ስራዎች ስኬታማነትና ለእንስሳት መኖ አቅርቦት መሻሻል ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢንስቲትዩቱ የትንበያ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አሳምነው ተሾመ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ፤ ተቋሙ የአየር ጸባይ አዝማሚያዎችን፣አዎንታዊና አሉታዊ ተጽዕኖዎችን በወቅቱ ለማህበረሰቡና ለሚመለከታቸው ተቋማት የማድረስ ስራውን በልዩ ትኩረት እየከወነ ይገኛል። ከየካቲት እስከ ግንቦት ባለው የበልግ ወቅትም፣ በተለይም በሀገሪቱ ደቡባዊ አጋማሽ የዓመታዊ ዝናብ መጠኑ እስከ 55 በመቶ የሚሸፈንበት ዋነኛ ወቅት ነው ብለዋል። በ2018 ዓ.ም የበልግ ወቅት አብዛኞቹ የአገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ እንደሚያገኙ ተናግረዋል፡፡ እስካሁንም በ55 የሚደርሱ አካባቢዎች በ24 ሰዓት ውስጥ ከ35 እስከ 148 ሚሊ ሜትር የሚደርስ ከፍተኛ መጠን ያለው ዝናብ መመዝገቡን ገልጸዋል። ባለፉት ቀናት የታየው ተስፋ ሰጪ የዝናብ ስርጭት ለአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች እንዳሉት ጠቅሰው፥ ለበልግ እርሻ ዝግጅትና ለዘር ስራ ምቹ ሁኔታን መፍጠሩንም ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ለሰውና ለእንስሳት የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ማሻሻሉን እንዲሁም የእንስሳት መኖ ልማትን በማፋጠን ረገድ ከፍተኛ ድርሻ መኖሩ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። በመጪዎቹ ሚያዝያና ግንቦት ወራትም በደቡብ፣ በደቡብ ምዕራብ፣ በመካከለኛውና በሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች የበልግ ዝናብ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በተለይም በደቡብና በደቡብ ምዕራብ አካባቢዎች ዝናቡ ዘግይቶ የሚወጣ በመሆኑ ለግብርናውና ለአካባቢ ጥበቃ ስራው ተጨማሪ ዕድል እንደሚፈጥር አስረድተዋል። ይሁን እንጂ፣ ከፍተኛ መጠን ያለው ዝናብ ወደ ጎርፍ አደጋ ሊቀየር ስለሚችል ማህበረሰቡና የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል።
በጣና ሐይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም ለማጥፋት አዲስ የንቅናቄ ዘመቻ ተጀመረ
Mar 25, 2026 192
ባህር ዳር ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ በጣና ሐይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም ለማጥፋት አዲስ የንቅናቄ ዘመቻ ተጀመረ። የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በሐይቁ ህልውና ላይ አደጋ የደቀነውን የእምቦጭ አረም በተደመረ አቅም ለማስወገድ የትብብር ጥሪ አቅርቧል። ከጣና ሃይቅና አካባቢው የእምቦጭ አረምን ለማስወገድ የሚያስችል የንቅናቄ መርሃ ግብር በባህር ዳር ከተማ ሽንብጥ ቀበሌ የጣና ዳርቻ በዛሬው እለት በይፋ ተጀምሯል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ሃላፊ አቶ ተስፋሁን አለምነህ፤ በጣና ሃይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም በተባበረ ክንድ በማስወገድ የሃይቁን ህልውና መጠበቅ ይገባናል ብለዋል። አረሙን ለማጥፋት በሰው ኃይል እና በማሽን እንዲሁም አጠቃላይ የሕዝቡን ጠንካራ ተሳትፎ ማእከል ያደረገ ስራ የሚጠይቅ መሆኑን ገልጸዋል። የእምቦጭ አረም በቀላሉ የመስፋፋትና የማንሰራራት ባሕሪ ያለው በመሆኑ ቀጣይነት ያለው ዘመቻ እና የክትትል ስራ የሚያስፈልግ ስለመሆኑም አፅኖት ሰጥተዋል። በመሆኑም በሐይቁ ህልውና ላይ አደጋ የደቀነውን የእምቦጭ አረም በተደመረ አቅም ለማስወገድ እንዘጋጅ በማለት ኃላፊው ጥሪ አቅርበዋል። የመከላከል ሥራው በሰው ኃይልና በማሽነሪ በመታገዝ እንዲሁም ከባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በባዮሎጂካል ዘዴ እየተከናወነ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።
ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ማሳካት በሚያስችል መልኩ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Mar 25, 2026 195
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ በ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ማሳካት በሚያስችል መልኩ ውጤታማ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ(ዶ/ር) ገለጹ። አስተባባሪው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ዘንድሮ የሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር፣ የመጀመርያው ምዕራፍ ማጠቃለያ ዓመት በመሆኑ ዝግጅቱ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡ በዚህም በዘንድሮው መርሃ-ግብር በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ በላይ ለመትከል እቅድ ተይዞ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት የተገኙ ተሞክሮዎችን በማስፋት የፍራፍሬ ችግኞችን የማስፋት፣ የሀገር በቀል ዝርያዎችን ቁጥር ከፍ የማድረግ ብሎም የእፅዋት አይነት ስብጥር በሰፊው እየተሰራበት መሆኑንም ገልፀዋል። በበጋው ወቅት የተከላ ቦታዎችን የመለየት፣ የተለዩ ቦታዎች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ የማከናወን፣ ከየአካባቢው አየር ንብረት ጋር የሚጣጣሙ ችግኞችን የማፍላትና የተለዩ ቦታዎች ላይ ካርታ የማዘጋጀት ስራ በስፋት መከናወኑን ነው ያስታወቁት። በዚህም በክልሎች እስካሁን 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ሄክታር መሬት ለችግኝ ተከላ የሚውሉ ቦታዎችን መለየታቸውን ጠቅሰው እስካሁን ከ110 ሺህ በላይ ችግኝ ጣቢያዎች ወደ ስራ ገብተው ችግኞች እያፈሉ ይገኛሉ ብለዋል። በዘንድሮው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ7 ነጥብ 5 ቢሊየን በላይ ችግኝ ለመትከል በእቅድ መያዙን ተናግረው እስካሁን 6 ነጥብ 1 ቢሊየን ችግኝ ዝግጁ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ በቀሪው ጊዜ የእንክብካቤ ተግባራት እንደሚከናወኑ ጠቅሰው ጉድጓድ የማዘጋጀት ስራዎችን ጨምሮ ሌሎችም እንደሚከናወኑ ገልጸዋል፡፡ ቀደም ሲል የነበረውን የክረምት ዝናብ ብቻ የመጠበቅ ልምድ መቀየሩን ጠቁመው ይህም ችግኞች ረጅም የዝናብ ወቅት እንዲያገኙ በማድረግ የፅድቀት መጠናቸውን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚጨምረው አስረድተዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አሁን ላይ የህዝቡ ባህል እየሆነ መምጣቱን ጠቅሰው በቀጣይም የዜጎችን የባለቤትነት ስሜት የማሳደግ እና የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።