ቀጥታ፡
አካባቢ ጥበቃ
አረንጓዴ ዐሻራ የሥነ-ምኅዳር ደህንነትን በማስተካከል ዕድገትን በማፋጠን ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ ነው
Jul 23, 2026 174
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2018 (ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን የሥነ-ምኅዳር ደኅንነት በማስተካከል ዕድገትን የሚያፋጥን ተጨባጭ ውጤት እያስገኘ መሆኑን የፌዴሬሽን ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ዛህራ ሁመድ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን "ተስፋን እንትከል" መሪ ሃሳብ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ሰኔ 8 ቀን 2018 ዓ.ም በቢሾፍቱ ሆራ አርሰዲ ሐይቅ ዳርቻ በይፋ ማስጀመራቸው ይታወሳል። በዚሁ የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይም፣ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ብልጽግና የሚያረጋግጥ ብሔራዊ የልማት ትልም መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮው መርሃ ግብር ስምንት ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት ሁሉም የማኅብረሰብ ክፍል በንቃት እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርበዋል። በዚሁ መሠረትም የተለያዩ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች፣ ሠራተኞችና የማኅበረሰብ ክፍሎች በየአካባቢያቸው ችግኝ በመትከል ዐሻራቸውን እያኖሩ ይገኛል።   የኢፌዴሪ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አመራርና ሠራተኞችም በአዲስ አበባ ለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ጎሮ የወንዝ ዳርቻ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሂደዋል። በዚሁ ወቅት የምክር ቤቱ ምክትል አፈ ጉባኤ ዛህራ ሁመድ፣ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን የሥነ-ምኅዳር ደኅንነት በማጠናከር ዘላቂ ልማትን የሚያፋጥን ተጨባጭ ውጤት እያስመዘገበ ነው ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መርሃ ግብሩ በ2011 ዓ.ም ከተጀመረ ወዲህ ባሉት ሰባት ተከታታይ ዓመታት በርካታ ቢሊዮን ችግኞች መተከላቸውን አስታውሰዋል። መርሃ ግብሩ የሥነ-ምኅዳር ሚዛንን ከማስጠበቅ ባለፈ የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲሁም ዛፍ መትከል ለሰው ልጆች የአዕምሮ እርካታና የልብ ደስታን በመፍጠር ተስፋን የማለምለም አቅም እንዳለው ጠቁመዋል። በተጨማሪም የተተከሉ ችግኞች ፀድቀው ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ መንከባከብና በቀጣይነት መከታተል የሁሉም ዜጋ ኃላፊነት መሆኑን አሳስበዋል።   በመርሃ ግብሩ የተሳተፉት የምክር ቤቱ የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር ተረፈ በዳዳ በበኩላቸው፣ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከሰው ልጆች ሕይወት ጋር ቀጥተኛ ቁርኝት ያለው የልማት ተግባር ነው ብለዋል። በዚህ ብሔራዊ ዘመቻ ላይ በመሳተፍ አሻራ ማኖር፣ በሀገር ልማትና በትውልድ ተስፋ ላይ አሻራ የማኖር ዕድል መሆኑንም ገልጸዋል። ዘንድሮ ለስምንተኛ ጊዜ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር መሳተፋቸውን የገለፁት ደግሞ ሌላኛዋ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ጽሕፈት ቤት የመንግሥታት ግንኙነት፣ የብዝኅነትና የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዳይሬክቶሬት ተጠባባቂ ዳይሬክተር መንደሪን ማርቆስ ናቸው።   መርሃ ግብሩ ለቀጣዩ ትውልድ ልምላሜን የተላበሰች ኢትዮጵያ ለማስረከብ ያለመ በመሆኑ፣ እስካሁን የተከሏቸውን ችግኞች በመንከባከብ እየተከታተሉ መሆኑን ገልጸዋል። የምክር ቤቱ የትራንስፖርት ባለሙያ አቶ ኬኔዲ መላኩ በበኩላቸው፣ ከልጅነት ጀምሮ ችግኝ የመትከል ልምድ እንዳላቸው ገልጸዋል።   ይህም ለተፈጥሮ ጥበቃና ለችግኝ እንክብካቤ ያላቸውን ግንዛቤ የበለጠ እንዲጎለብት አስችሎኛል ብለዋል።
የፅዱ ኢትዮጵያ ኢኒሼቲቭ ከተሞችን ውብ፣ ፅዱ፣ ለኑሮ እና ለቱሪዝም ፍሰት የተመቹ እንዲሆኑ አድርጓል
Jul 23, 2026 205
ባህር ዳር ፤ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፡-የፅዱ ኢትዮጵያ ኢኒሼቲቭ ከተሞችን ውብ፣ ፅዱ ፣ ለኑሮ እና ለቱሪዝም ፍሰት የተመቹ በማድረግ የተሻለ ውጤት እንዲመዘገብ ማድረጉን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለፀ። ''ፅዱ ኢትዮጵያ ለትውልድ'' በሚል መሪ ሀሳብ የሦስተኛ ዙር ክልል አቀፍ የአካባቢ ብክለት መከላከል ዘመቻ የንቅናቄ ማስጀመሪያ ፕሮግራም በባህር ዳር ከተማ ተካሂዷል።   የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬነሽ መኩሪያ በመድረኩ እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የሚያስችሉ ስራዎች በልዩ ትኩረት እየተከናወኑ ይገኛል። በተለይ ከለውጡ ዓመታት ወዲህ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል የሚያስችሉ ወሳኝ ፖሊሲዎችን፣ አዋጆችን፣ መመሪያዎችንና ደንቦችን አውጥቶ በመተግበር ውጤታማ ስራ ማከናወን መቻሉን ገልፀዋል። በአሁኑ ወቅትም በከተሞች በስፋት እየተከናወነ ያለው የኮሪደር እና የወንዝ ዳርቻ ልማት፣የአረንጓዴ አሻራና መሰል የልማት ስራዎች ለፅዱ ኢትዮጵያ መጠናከር ሰፊ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም በሃይቆች፣ ወንዞችና ሌሎች የውሃ አካላት ብሎም በመኖሪያ አካባቢዎች ለማሕበረሰቡ ጤና አደገኛ የሆኑ የፕላስቲክ ውጤቶችን በማስወገድ በኩል ምሳሌ የሚሆን ስራ መሰራቱን አረጋግጠዋል። መንግስት የአካባቢ ጥበቃን ለዘላቂ ልማትና መጭውን ትውልድ ታሳቢ በማድረግ እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለበለጠ ውጤታማነት በተሻለ ትብብር መስራት ይገባል ብለዋል። ''ፅዱ ኢትዮጵያ ለትውልድ'' ሦስተኛው ዙር ንቅናቄ የፕላስቲክ ውጤቶችን በማስወገድ፣ የድምፅ ብክለትን በመከላከል እና የብዝሃ ህይወት መመናመን እና የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል በሚያስችሉ ተግባራት ላይ ህብረተሰቡን እያሳተፈ ይገኛል። የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ኃላፊ አቶ በልስቲ ፈጠነ በበኩላቸው፤ በፅዱ ኢትዮጵያ ኢኒሼቲቨ በርካታ ውጤታማ ስራዎችን ማከናወን ተችሏል። በተለይም ጣና ሀይቅንና ሌሎች የውሃ አካላትን ከፕላስቲክ ቆሻሻና ሌሎች በካይ ነገሮች በማፅዳት የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል ነው ያሉት። አሁን ላይ የፕላስቲክ ውጤቶችን በመሰብሰብና መልሶ መጠቀም የሀብት መፍጠሪያ መሆኑን አመልክተው ፤የአካባቢ ብክለትን በዘላቂነት በመከላከል ምቹ የኑሮ አካባቢ በመፋጠር የተጀመሩ ስራዎች ተጠናከረው ይቀጥላሉ ነው ያሉት። መንግስት በአካባቢ ጥበቃ ስራዎች ከሀገር አልፎ ለአህጉርና ዓለም አቀፋ መድረክ ምሳሌ የሚሆን ስራ እየሰራ ነው ያሉት ደግሞ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ልዩ አማካሪ አቶ ይትባረክ አወቀ ናቸው። በፅዱ ኢትዮጵያ ከተሞችን በመግለጥና ለቱሪዝም ዘርፉ ማደግ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅስው ይህ ንቅናቄም በተገቢው መንገድ እንዲተገበርና ተጠናክሮ እንዲቀጥል ክትትልና ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል። በመድረኩ የፌዴራል፣ የክልል፣ የዞንና ከተማ አስተዳደር አመራሮችና ባለሙያዎች ብሎም ባለድርሻ አካላት የተገኙ ሲሆን በባህር ዳር ከተማ የፅዳት ዘመቻና የፓናል ውይይት ተከናውኗል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ ከመትከል ባሻገር ለትውልድ የሚተርፍ አርዓያነት ያለው ተግባር ነው
Jul 23, 2026 159
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ ከመትከል ባሻገር ለትውልድ የሚተርፍ አርዓያነት ያለው ተግባር መሆኑን የመገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሀይማኖት ዘለቀ ገለጹ። የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለሥልጣን ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሀሳብ የዘንድሮውን የክረምት አረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በቤላ 18 ቀበሌ የወንዝ ዳርቻ አካሂዷል።   በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሀይማኖት ዘለቀ፣ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ ከመትከል ባለፈ ለመጪው ትውልድ ታሪክ የምናኖርበት አርአያነት ያለው ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። የችግኝ ተከላው የኢትዮጵያን የደን ሽፋን ከማሳደግ፣ የአየር ንብረት ለውጥን ከመቋቋም እና የግብርና ምርታማነትን ከማሻሻል አንጻር ትልቅ ሀገራዊ ፋይዳ እንዳለውም ተናግረዋል። በመሆኑም ትኩረታችን ችግኝ መትከል ላይ ብቻ ሳይወሰን፤ የተተከሉትን በማሳደግ፣ በመንከባከብ እና የፅድቀት መጠናቸውን በማረጋገጥ ላይ ሊሆን ይገባል ሲሉም አሳስበዋል።   መርሃ ግብሩ ለምግብ ዋስትና የሚረዱ የፍራፍሬ እና ለአካባቢ ጥበቃ ጠቀሜታ ያላቸው የዛፍ ዝርያዎችን ያካተተ መሆኑንም ገልጸዋል። መገናኛ ብዙሃን መረጃን ለሕብረተሰቡ ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ ሀገራዊ የደን ሽፋን ጥረትን ለመደገፍ ያላቸውን ኃላፊነት ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ባለሥልጣኑ በ8ኛው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 45 ሺህ 125 ችግኞችን ለመትከል አቅዶ እየሰራ ሲሆን፣ እስካሁን በተለያዩ የከተማዋ አካባቢዎች ከ43 ሺህ በላይ ችግኞች መተከላቸው ተገልጿል።
ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች የእንጦጦ - ቀበናን የወንዝ እና የወንዝ ዳር ፕሮጀክት ጎበኙ
Jul 23, 2026 240
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2018(ኢዜአ)፦የብልፅግና ፓርቲ ዋናው ማዕከል እና የክልል ቅ/ፅህፈት ቤት በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች በመዲናዋ በመፍጠር እና በመፍጠን የተገነቡ የወንዝ ዳር ልማት ፕሮጀክቶችን ተዟዙረዉ ጎብኝተዋል። የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት እና የዋናው ማዕከል ኃላፊ አቶ አደም ፋራህ እና ሌሎችም የፌዴራል፣ የአዲስ አበባ እና የክልል ከፍተኛ አመራሮች በጉብኝቱ ተሳትፈዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በጉብኝቱ ማጠቃለያ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፤ የብልፅግና ፓርቲ ምናብ ወደ ውጤት እየተቀየረባት የምትገኘው ውቧ መዲናችን ሁሌም አዲስ እየሆነች ትገኘለች ብለዋል። አዲስ አበባ የብልፅግና አይቀሬነት ማሳያ መሆኗን የገለፁት ከንቲባ አዳነች ተግተን በመሥራት በላቁ አዳዲስ ድሎች እንገናኛለን ብለዋል።   በብልፅግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅ/ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ በበኩላቸው፤ የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክቶች የከተማዋን ገፅታ ከመገንባታቸው ባሻገር የሕዝቡን የኑሮ ደረጃ ከፍ ማድረጋቸውን አስረድተዋል።   ከፍተኛ አመራሮች 10.5 ኪሎ ሜትር የሚረዝመውን፣ አረንጓዴ ቦታዎች፣ የህፃናት መጫወቻዎች፣ የወጣቶች የስፖርት ማዘውተሪያዎች፣ ሱቆች፣ ካፍቴሪያዎች፣ ቤተ መፅሀፍት ፣ የከተማዋ ነዋሪ አንዱ የመዝናኛ ማዕከል የሆነውን የቀበና ግድብ እና ሌሎችም የህዝብ መገልገያዎች ያሉትን የእንጦጦ - ቀበና የወንዝ ዳር ፕሮጀክትን ተዟዙረዉ መጎብኘታቸውን ከከንቲባ ጽ/ቤት የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡
በቀጣዮቹ አስር ቀናት የተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ከቀላል እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ
Jul 22, 2026 164
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦በቀጣዮቹ አስር ቀናት የተለያዩ የሀገሪቷ ክፍሎች ከቀላል እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ መሰረት፣ ከሐምሌ 14 እስከ ሐምሌ 24 ቀን 2018 ዓ.ም ባሉት አስር ቀናት ውስጥ የዝናብ ሁኔታን የሚፈጥሩ ሁኔታዎች የበለጠ እየተጠናከሩ እንደሚሄዱ አሰታወቋል። በዚህም መሰረት በደቡብ ምዕራብ፣ ምዕራብ፣ ሰሜን ምዕራብ፣ ሰሜን፣ መካከለኛው፣ ሰሜን ምስራቅ እና ምስራቅ የሀገሪቷ ክፍሎች የተሻለ የዝናብ ሥርጭት መጠን ይኖራቸዋል። በደቡብ ምዕራብ፣ ምዕራብ፣ ሰሜን ምዕራብና ሰሜን የሀገራችን አካባቢዎች ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ገልጿል። በተጨማሪም በመካከለኛው፣ ሰሜን ምስራቅ፣ ምስራቅ እና ደቡብ የሀገሪቷ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖራቸው አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች ያመለክታሉ ብሏል። በሚቀጥሉት አስር ቀናት የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ የሆኑ የሀገሪቱ አብዛኛዎቹ አካባቢዎች ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙም ነው ኢንስቲትዩቱ የጠቆመው። በደቡብ ምዕራብ፣ ምዕራብ፣ ሰሜን ምዕራብ፣ ሰሜን እና በመካከለኛው የሀገሪቷ አካባቢዎች ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ገልጿል። በተጨማሪም በኤሊ ዳር፣ ዱብቲ፣ ሰመራ፣ ቡሬ፣ አሳይታ፣ ሁንዱፎ፣ ገዋኔ፣ ሚሌ፣ ዳሊፋጊ፣ አይሻ፣ ጉሊና፣ አዋሽ አርባ፣ ባቲ፣ ዶሎ አዶ፣ ዳዋ፣ አሶሶ፣ ጎዴ፣ ቋራ፣ አዋሽ ፈንታሌ፣ ጭፍራ፣ ላሬ፣ መተሀራ እና፣ ላሬ፣ ፉኙዶ አካባቢዎች ከሚኖረው የቀን ከፍተኛ የፀሀይ ሀይል ጋር ተያይዞ ከፍተኛ ሙቀት ይኖራቸዋል። ኢንስቲትዩቱ በቀጣይ ቀናት የሚኖረውን መልካም አጋጣሚዎችን ለመጠቀም እና የሚጠበቁ አሉታዊ ተጽዕኖዎችን ለመከላከል የግብርና ሚቲዎሮሎጂ ምክር ሀሳብን ከወዲሁ መተግበር እንደሚያስፈልግ አሳስቧል።
ወጣቶች በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ላይ መሳተፋቸው የእርስ በርስ ግንኙነትን ለማጎልበት ያግዛል
Jul 22, 2026 181
ደብረብርሃን ፤ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦ወጣቶች በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ላይ መሳተፋቸው የእርስ በርስ ግንኙነትን ለማጎልበት ያግዛል ሲሉ የወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተሳታፊ ወጣቶች ገለጹ። ወሰን ተሻጋሪ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶችን ያሳተፈው የክረምት የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ -ግብር በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ጠባሴ ክፍለ ከተማ በሚገኘው የኢንዱስትሪ መንደር ዛሬ ተጀምሯል። ወጣቶቹ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞች ለኢትዮጵያ እድገትና ብልጽግና መሰረት የሚጥሉ በመሆናቸው ተሳታፊነታችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። ከበጎ ፈቃደኛ ወጣቶቹ መካከል ከጌዲዮ ዞን ዲላ ከተማ የመጣችው ወጣት ትንሳኤ ትዕዛዙ እንደገለጸችው፤ የአገራችን ከፍታ የሚረጋገጠው አንድነታችን በመጠበቅ ለጋራ አላማ በአንድነት ስንቆም ነው። የወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከሁሉም አካባቢዎች የተሰባሰቡ ወጣቶች የአረንጓዴ አሻራቸውን በማስቀመጥ የሀገር አንድነትና እድገትን ለማጽናት የምንሰራበት ነው ስትል አንስታለች። ከድሬደዋ ከተማ አስተዳደር የመጣው ወጣት አላዛር ታሪኩ በበኩሉ ፤በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በጋራ የሚተከሉት ችግኞች በህዝቦች መካከል መቀራረብን፣ አብሮነትንና አንድነትን ለማጠናከር የሚያስችሉ ናቸው ብሏል።   ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ ስራ ወጣቱ የተለያዩ አካባቢዎች ባሀል፣ ወግና እሴትን እንዲረዳ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ነው የተናገረው። በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ የተከልናቸው ችግኞች አገራዊ አንድነትና ትብብርን ለማጠናከር የሚያግዙ ናቸው ያለችው ደግሞ ከአማራ ክልል ኦሮሞ ብሄረሰብ አስተዳደር ከሚሴ ከተማ የመጣችው ሰዓዳ ኢንድሪስ ናት። በተለይም በህዝቦች መካከል በተሳሳተ ትርክትን በማጥፋት ዘላቂ ፍቅርን፣ ሰላምና ልማትን ለማጎልበት የሚያስችል ነው ስትል ተናግራለች። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በከተማዋ ተስማሚ የአየር ንብረትና ስነ ምህዳር ለመጠበቅ ሰፊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። በተለይም እየተስፋፋ የመጣው የኢንዱስትሪ ልማትና የኢንቨስትመንት ፍሰትን ይበልጥ ለማሳደግ የላቀ ድርሻ እንደሚኖረው ነው የገለጹት። የተተከሉ ችግኞችን ተንከባክቦ ለታለመለት ግብ በማብቃት ከተማዋን ለነዋሪዎችና ጎብኚዎች የተመቸች ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል። ወሰን ተሻጋሪ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የሚሰጡ ወጣቶች በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ላይ መሳተፋቸው አንድነት፣ ሰላምና ፍቅርን ይበልጥ ለማጎልበት እንደሚረዳም ነው የተናገሩት። የደብረ በርሃን ከተማ አስተዳደር ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ መርሻ አይሳነው በበኩላቸው፤ በተያዘው የክረምት ወቅት ዘጠኝ ነጥብ አንድ ሚሊዮን የሚሆኑ የደን፣ የውበትና ኢኮኖሚያዊ ጥቅም የሚሰጡ ችግኞች እየተተከሉ ነው ብለዋል። በዘንድሮው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከሁለት ሺህ 300 ሄክታር መሬት በላይ ለመሸፈን እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው ባለፉት ዓመታት የለሙ አካባቢዎች አሁን ላይ ጥቅም መስጠት እንደጀመሩም ተናግረዋል።
በዞኑ ከ26ሺ ሔክታር  መሬት ላይ  የተሻሻሉ የቡና ችግኞች እየተተከሉ ነው
Jul 22, 2026 147
መቱ፣ሐምሌ 15/2018(ኢዜአ):- በኢሉባቦር ዞን በተያዘዉ ክረምት ከ26 ሺህ ሄክታር በላይ በሆነ መሬት ላይ ዝርያቸው የተሻሻሉና በአጭር ጊዜ ምርት የሚሰጡ የቡና ችግኞች እየተተከሉ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ አዳሙ ታከለ እንደተናገሩት፤በዞኑ በሽታን የሚቋቋሙ፣ በአጭር ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጡ እና ምርታማነታቸው የተረጋገጠ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በማቅረብ የተከላ ስራ እንዲጀመር ተደርጓል። በዚሁ መሰረት በተያዘው የክረምት ወቅትም ከ26ሺ ሔክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ ከ200 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኝን የመትከል ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል።   በዚሁ ወቅት የቡና ምርትና ምርታማነትን ለመጨመር እንዲቻል ልማቱን የማስፋትና የእንክብካቤ ስራዎችም እንዲጠናከሩ እየተደረገ ነው ብለዋል። በአዲስ መሬትና በደረቁ የቡና ተክሎች ምትክ የቡና ችግኝ የመትከል ሥራ በሰፊው እየተከናወነ ሲሆን፣ ያረጁና ምርት የማይሰጡትን በመጎንደል ውጤታማ ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ የሁሩሙ ወረዳ አርሶ አደር ታምሩ ፈሪሳ ፤ከቡና ልማቱ በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ ለመሆን በበጋው ወቅት የጎነደሏቸውን የቡና ተክሎች በመንከባከብ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት የቡና ልማቱን በማስፋት ይበልጥ ተጠቃሚ ለመሆን የተሻሻሉ የቡና ችግኞችን እየተከሉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። አርሶ አደር ጌታቸው ጂፋርም በግብርና ባለሙያዎች በመታገዝ የቡና ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ ተግባራት ላይ መሰማራታቸውን ነው የሚገልጹት። በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም የተሻሻሉ የቡና ችግኝን በስፋት በመትከል ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። በኢሉባቦር ዞን ከ72 ሺ በላይ አርሶ አደሮች በቡና ልማት ላይ ተሰማርተው የሚገኙ መሆናቸውን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።    
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአፍጥር የተፈጥሮ ደን ተጠብቆ ለትውልድ እንዲሸጋገር እያስቻለ ነው
Jul 22, 2026 248
ወልቂጤ ፤ ሐምሌ 15/2018 (ኢዜአ)፦ በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአፍጥር የተፈጥሮ ደን ተጠብቆ ለትውልድ እንዲሸጋገር እያስቻለ መሆኑን የወረዳው ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የአፍጥር የተፈጥሮ ደን በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በጉራጌ ዞን ቸሃ ወረዳ ከሚገኙ የተፈጥሮ ደኖች ከቀዳሚዎች መካከል ይጠቀሳል።   ደኑን በመጠበቅ ብዝሃ-ህይወትን ለማቆየትና የአየር ጸባይ ለውጥን ለመከላከል እንዲሁም ለአካባቢው ማህበረሰብ የሚኖረውን ኢኮኖሚና ማህበራዊ ፋይዳ ለማጉላት እየተሰራ ነው። ተግባሩን ለማስቀጠልም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ትልቅ አጋዥ ሆኖ እያገለገለ መሆኑም ተጠቅሷል።   የቸሃ ወረዳ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጠቅልል አባድየ እንዳሉት 40 ሄክታር መሬት የሚሸፍነው የአፍጥር ደን ከሰውና እንስሳት ንክኪ ነጻ እንዲሆን ጥበቃ እየተደረገለት ነው። ደኑ የአካባቢውን የስነ-ምህዳር ሚዛን እንዲጠበቅና ወጣቶች በደኑ በንብ ማነብ እንዲሁም በመኖ ሳር ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። ደኑ ለአፍጥር ከተማም ውበትና የመስህብ ስፍራ በመሆን እያገለገለ መሆኑን አመልክተዋል። የደን ጥበቃው የአፈር መሸርሸርን ከመከላከል ባለፈ ለከርሰ-ምድር ውሃ ምንጭነት ያለውን አቅም ለማስቀጠል በክፍት ቦታዎች ላይ ችግኝ የመትከልና የመንከባከብ ስራ መከናወ ኑን ጠቅሰዋል። ህዝቡ ለደኑ ጥበቃና እንክብካቤ ከማድረግ ባለፈ ሳሳ ባሉ የደኑ ክፍሎች ​የሀገር በቀል ዛፎች እየተከለ መሆኑን ያነሱት ​ደግሞ በአፍጥር ደን ዙሪያ ከሚገኙ ነዋሪዎች መካከል አቶ ደንጭዛ ጃጃተ ናቸው።   እንደ ዝግባ፣ ጽድ፣ ዋንዛና ሌሎች የሀገር በቀል ዛፎች ጥበቃ የማድረግ ማህበረሰባዊ እሴትም ለስራው ውጤታማነት ማገዙን ተናግረዋል። ​የአካባቢው ማህበረሰብ ደንን ጠብቆ ለቀጣዩ ትውልድ የማስተላለፍ ባህልን ከአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ጋር በማጣመር እየሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ አቶ ፍቃዱ አመርቻ ናቸው።   በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ደኑን በመንከባከብና በክፍት ቦታዎች ላይ ሃገር በቀል ችግኝ በመትከል ወደ ቀጣዩ ትውልድ ለማሻገር እየሰራን ነው ብለዋል፡፡ ዘጠኝ ሆነው በመደራጀት የሃገር በቀል ዛፎች ችግኝ በማፍላትና በማዘጋጀት ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር እያቀረቡ መሆናቸውን የገለጸው ደግሞ ወጣት ያለው ተረጋ ነው። በአካባቢው ተግባራዊ እየተደረገ ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር የገበያ እድል እንደፈጠረላቸውና የአፍጥር ደንም ለሚያዘጋጇቸው ችግኞች የዘር ምንጭ መሆኑን አመልክቷል።
ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ለዓለም ያበረከተችው ታሪካዊ ዕሴት በአርዓያነት የሚጠቀስ ነው 
Jul 21, 2026 223
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፦ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ለዓለም ያበረከተችው ታሪካዊ ዕሴት በአርዓያነት የሚጠቀስ መሆኑን የዓለም አቀፍ የተፈጥሮ ጥበቃ ሕብረት (IUCN) የዝርያዎች ሕልውና ኮሚሽን ሊቀመንበር ቪቬክ ሜኖን (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን 60ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል "60 ዓመታትን ለኢትዮጵያ የዱር ሕይወት" በሚል መሪ ሐሳብ በአዲስ አበባ ተካሂዷል። በመድረኩ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትርና የኃይለማርያምና ሮማን ፋውንዴሽን የቦርድ ሰብሳቢ ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና የዓለም አቀፍ ተቋማት ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።   የዓለም አቀፍ የተፈጥሮ ጥበቃ ሕብረት (IUCN) የዝርያዎች ሕልውና ኮሚሽን ሊቀመንበር ቪቬክ ሜኖን (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ ለዓለም ያበረከተችው ታሪካዊ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ባህልና ቅርስ በአርዓያነት የሚወሰድ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳትና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ታሪክ ጥቂት አሥርተ ዓመታትን ብቻ ሳይሆን በርካታ ክፍለ ዘመናትን ወደ ኋላ የሚመልስ ጥንታዊ መሠረት ያለው መሆኑን አስታውቀዋል። ኢትዮጵያ ገና በ15ኛው ክፍለ ዘመን በንጉሥ አፄ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥት ጀምሮ የመናገሻ ደንን በመጠበቅና በማወጅ የተፈጥሮ ሀብቷን መንከባከብ የጀመረች ሀገር መሆኗን አንስተዋል። ይህም እርምጃ ደኖችና ተፈጥሮ ለዓለም ሕልውና ያላቸውን ከፍተኛ አስፈላጊነት ቀድማ ያወቀችና ጥንታዊ የነቃ አስተዳደርነትን ያሳየች ሀገር መሆኗን ማረጋገጫ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያም ተፈጥሮዋን ለማስጠበቅ እያደረገች ያለችው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም አስታውቀዋል። የዱር እንስሳትና ብዝኃ ሕይወት ከሥነ-ምህዳር ጋር ጥብቅ ቁርኝት አላቸው ያሉት ሊቀመንበሩ፤ ያለ ዝርያዎች ሕልውናና ያለ ብዝኃ ሕይወትሥነ-ምህዳርን በብቸኝነት መጠበቅ እንደማይቻል አስገንዝበዋል። አብዛኞቹ የዓለማችን ድንቅ ፍጥረታት የሚገኙት በምሥራቁ የዓለም ክፍል፣ በተለይም በአፍሪካ እና በእስያ አህጉራት በመሆኑ ዓለም የነዚህን አህጉራት ተፈጥሮ የመጠበቅና የመንከባከብ ከፍተኛ ታሪካዊ ኃላፊነት እንዳለበት አሳስበዋል። የIUCN የዝርያዎች ሕልውና ኮሚሽን በአሁኑ ወቅት በዓለም ዙሪያ የሚገኙ ከ12,000 በላይ ገለልተኛ ሳይንቲስቶችንና ባለሙያዎችን በአባልነት አቅፎ እየሠራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፍ የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ እያበረከተችው ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው
Jul 21, 2026 168
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፍ የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ እያበረከተችው ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት የብዝሃ ሕይወት ስምምነት (CBD) አስፈጻሚ ጸሀፊ አስትሪድ ሾማከር ገለጹ። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን 60ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን እያከበረ ነው፡፡ በመድረኩ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትርና የኃይለማርያምና ሮማን ፋውንዴሽን የቦርድ ሰብሳቢ ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና የዓለም አቀፍ ተቋማት ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል። የተባበሩት መንግሥታት የብዝሃ ሕይወት ስምምነት (CBD) አስፈጻሚ ጸሀፊ አስትሪድ ሾማከር ፣ ኢትዮጵያ የበርካታ፣ ልዩ የእፅዋትና የእንስሳት ዝርያዎች መገኛና የብዝሃ ሕይወት ማዕከል መሆኗን ተናግረዋል። ሀገሪቱ ለዓለም አቀፍ የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ እያበረከተች ያለው ሚና እጅግ ጉልህ መሆኑንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በዓለም ላይ በሌላ ቦታ የማይገኙ ብርቅዬ ዝርያዎች ባለቤት መሆኗን ጠቅሰው፤ ይህ ልዩ የተፈጥሮ ቅርስ ለኢትዮጵያ ኩራት ብቻ ሳይሆን ለመላው ዓለም ሊተመን የማይችል እሴት እንዳለው ተናግረዋል። ባለፉት ስድስት አስርት ዓመታት የተፈጥሮና የብዝሃ ሕይወት ቅርሶችን ለመጠበቅ ተቋሙ ላሳየው ቁርጠኝነትም አድናቆታቸውን ገልጸዋል። ሀገሪቱ የጥበቃ ቦታዎችን በሚገባ በማስተዳደር፣ አደጋ ላይ ያሉ ዝርያዎችን በመታደግ እና በሰውና በዱር እንስሳት መካከል የሚፈጠሩ ግጭቶችን ለመቆጣጠር ያደረገችው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን አብራርተዋል። የተቀመጡ የብዝሃ ሕይወት ግቦችን ስኬታማ ለማድረግ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የደን ሀብትን በመጠበቅ፣ ዝርያዎችን ከአደጋ ለመታደግ እና ሕገወጥ የዱር እንስሳት ንግድን ለመቆጣጠር የተፋጠነ እርምጃ መውሰድ እንዳለበት አስገንዝበዋል።
ባለሥልጣኑ የዱር እንስሳት ሀብትን በዘላቂነት ለመንከባከብና ዓለምአቀፍ ትብብርን ለማሳደግ በርካታ ተግባራትን አከናውኗል
Jul 21, 2026 180
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን የዝርያ ጥበቃን ለማጠናከር፣ የዱር እንስሳት ሀብትን በዘላቂነት ለመንከባከብና ዓለምአቀፍ ትብብርን ለማሳደግ በርካታ ተግባራት ማከናወኑን ለአደጋ የተጋለጡ የዱር አራዊትና ዕፅዋት ዝርያዎች ዓለምአቀፍ ንግድ ስምምነት (CITES) ዋና ፀሐፊ ኢቮን ሂጌሮ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን 60ኛ ዓመት የምስረታ በዓል "60 ዓመታትን ለኢትዮጵያ የዱር ሕይወት" በሚል መሪ ሀሳብ በደማቅ ሁኔታ እየተከበረ ይገኛል። በበዓሉ ላይ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ፣ የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ፣ እንዲሁም አምባሳደሮች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።   ለአደጋ የተጋለጡ የዱር አራዊትና ዕፅዋት ዝርያዎች ዓለም አቀፍ ንግድ ስምምነት (CITES) ዋና ፀሐፊ ኢቮን ሂጌሮ በዚሁ ወቅት፤ ባለሥልጣኑ ባለፉት ዓመታት የዝርያዎች ጥበቃን ለማጠናከር፣ ሕገ-ወጥ የዱር እንስሳት ንግድን ለመከላከልና ዓለም አቀፍ ትብብርን ማሳደግ ያስቻሉ በርካታ ተግባራት ማከናወኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ1989 ስምምነቱን ከተቀላቀለችበት ጊዜ ጀምሮ ከሴክሬተሪያቱ ጋር ላላት የረጅም ጊዜ አጋርነት ከፍተኛ አድናቆት እንዳላቸውም ገልጸዋል፡፡ ባለሥልጣኑ በባቢሌ የዝሆኖች መጠለያ፣ በጋምቤላ ብሔራዊ ፓርክ እና በሌሎችም መሠረተ-ልማቶች በሚገኙ የክትትል ጣቢያዎች በኩል ዝሆኖችን ለመቆጣጠር የሚረዳ ጠቃሚ መረጃን ለአለም አቀፉ ማኅበረሰብ ሲያካፍል ቆይቷል ብለዋል። እነዚህ ስኬቶች የባለሥልጣኑ ሠራተኞች፣ ሬንጀሮችና የአካባቢው ማኅበረሰብ አጋሮች ከአፍሪካ ዝሆን እስከ ጭላዳ ባቡን እና ብርቅዬ እንስሳት ጥበቃ ያደረጉት የማያቋርጥ ጥረት ማሳያ መሆናቸውን ገልጸዋል። የ2030 የዘላቂ ልማት ግቦችን ለማሳካት ከኢትዮጵያ ጋር ያለው ትብብር እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል፡፡
የአረንጓዴ ዐሻራ የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በመጠበቅ የዱር ሕይወት መጠጊያና መኖሪያ የሚያገኙበትን ወሳኝ ዕድል ፈጥሯል
Jul 21, 2026 233
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በመጠበቅ የዱር ሕይወት መጠጊያና መኖሪያ የሚያገኙበትን ወሳኝ ዕድል መፍጠሩን የኢፌድሪ ፕሬዝደንት ታዬ አጽቀስላሴ ገለጹ። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን 60ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል "60 ዓመታትን ለኢትዮጵያ የዱር ሕይወት" በሚል መሪ ሐሳብ በአዲስ አበባ ተካሂዷል።   የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለዘመናት ያከማቸችውን የዱር ሕይወት ጥበቃ ከትውልድ ወደ ትውልድ በማሸጋገር ከአፍሪካ ግንባር ቀደም እንደሚያደርጋት ገልጸዋል። የኢትዮጵያውያን የዱር ሕይወት ጥበቃ ባህላዊ ሥርዓትም ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፍ አስደናቂ ዕሴት መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት መለያ የሆነው የዋሊያ አይቤክስ መመናመን አሳሳቢ ነው ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ ይህንን ለመታደግ ሀገራዊና ዓለም አቀፋዊ ግዴታ አለብን ብለዋል። በአንዳንድ አካባቢዎች በአጉል ልማድና ኋላ ቀር አስተሳሰብ በመነሳት በዱር እንስሳት ላይ የሚደርሰውን ጥፋት በማስቆም ጸጋዎችን አጥብቆ መያዝ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በሀገራዊ ለውጡ ማግስት ባለፉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ የተፈጥሮ ሀብቶችንና የብዝኃ ሕይወት ሥነ-ምህዳር ሚዛንን ለመጠበቅ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን አንስተዋል። የኢትዮጵያ አረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርም የደረቁ ምንጮችንና ደኖችን በመመለስ ሸሽተውና ጠፍተው የነበሩ የዱር እንስሳት መጠጊያና መኖሪያነት እያገለገሉ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ይህም በአጭር ጊዜ ውስጥ የታየ እውነታ መሆኑን በማንሳት። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ሁለንተናዊ ስኬት እንዲመዘገብ በማስቻል ለብዝኃ ሕይወት ደኅንነት ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋና አቅርበዋል። ቀደም ሲል ከነበረው ልማዳዊ አሠራር ሰንሰለት በመላቀቅ በብሔራዊ ፓርኮች ልማት አዲስ ሕይወትና እይታ ለመስጠት የተደረገው ርብርብ ትልቅ እመርታ ማምጣቱንም ጠቁመዋል። የፓርኮችን ደኅንነት ማረጋገጥ እና መሠረተ ልማቶቻቸውን ማዘመን ለዱር ሕይወት ጥበቃ ብቻ ሳይሆን የሀገር ውስጥ እና የውጭ ጎብኚዎችን ለመሳብ ለሚደረገው ጥረት ቁልፍ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል። በከተሞች እየተገነቡ ያሉ ፓርኮችም ሕብረተሰቡ ለዱር ሕይወት ያለውን የእውቀት አድማስ የሚያሰፉ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዘርፉ የሚጠበቀውን ውጤት ለማምጣት ተግቶ መስራት እንደሚገባ ጠቁመው፤ ባለፉት ስልሳ ዓመታት ባለሥልጣኑ እንዲሁም አጋር አካላት ተፈጥሮን ለመጠበቅ ላበረከቱት ጉልህ አስተዋጽኦ ምስጋና አቅርበዋል። በመድረኩ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትርና የኃይለማርያምና ሮማን ፋውንዴሽን የቦርድ ሰብሳቢ ኃይለማርያም ደሳለኝ፣ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ እንደገና አበበ (ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና የዓለም አቀፍ ተቋማት ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል።
የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና ልማትን በማጠናከር ለነገው ትውልድ የተሻለች ሀገር ለማስረከብ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jul 21, 2026 157
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና ልማትን በማጠናከር ለነገው ትውልድ የተሻለች ሀገር ለማስረከብ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ ገለጹ። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን 60ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን እያከበረ ነው፡፡   በክብረ በዓሉ ላይ የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ፣ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች፣ የዓለም አቀፍ ተቋማት ተወካዮችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ በዚሁ ወቅት፤ ተፈጥሮ ለኛ ከተሰጠ ሀብትነት ባሻገር ለመጭው ትውልድ የምናስተላልፈው አደራ ጭምር ነው ብለዋል፡፡ በመሆኑም የተፈጥሮ ሀብትን መጠበቅ አማራጭ ሳይሆን ግዴታ መሆኑን ጠቅሰው ተራሮች፣ ሰፋፊ ወንዞች፣ ረግረጋማ ቦታዎች፣ ጥልቅ ሸለቆዎች እና ሀይቆች የኢትዮጵያ ብዝሃ ሕይወት ሀብት መለያዎች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ዋልያ አይቤክስ፣ ቀይ ቀበሮ፣ ጭላዳ እንዲሁም በርካታ አእዋፋትና አበቦች በተፈጥሮ ሀብታችን የታደልናቸው የሀገራችን ማንነት እና የኢኮኖሚያችን አቅም ናቸው ሲሉም ተናግረዋል፡፡ የዱር ህይወት ጥበቃ በኢትዮጵያ ከዘመናዊ ተቋማዊ አደረጃጀት በፊት በባህላዊና ማህበራዊ እሴቶቻችን ውስጥ ዘመን የተሻገረ፣ ስር የሰደደ እና የማህበረሰብ ጥበቃ ተሞክሮዎች ለዛሬው ጥበቃ መሰረቶች መሆናቸውን ገልጸዋል። ከ60 ዓመታት በፊት በሁለት ብሔራዊ ፓርኮች የተጀመረው ዘመናዊ የጥበቃ ጉዞ፣ ዛሬ ላይ እንደ ሀገር ከ30 በላይ መድረሳቸውን ጠቁመዋል፡፡ በርካታ የዱር እንስሳት መጠለያዎች ከ106 በላይ ልዩ ልዩ የዱር እንስሳት ጥበቃ ቦታዎች መፈጠራቸውን ተናግረዋል፡፡   ዛሬ እንደ ሰፊ የጥበቃ ቦታዎች አስተዳደር፣ የብሔራዊ ፓርኮች ልማት፣ የብዝሀ ሕይወት ጥበቃ፣ ዘላቂ ቱሪዝም እና የማህበረሰብ ተሳታፊነት የተመሰረተበትን ልማት ማረጋገጥ መቻሉን አመላክተዋል፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የጥበቃ ቦታዎች አስተዳደር እንዲጠናከር፣ የአካባቢው ማህበረሰብ ተሳታፊነት እንዲያድግ፣ የቱሪዝም መሰረተ ልማቶች እንዲሻሻሉ እና ዲጂታል ቴክኖሎጂዎች በጥበቃ ስራ ውስጥ በስፋት እንዲተገበሩ መደረጉን አንስተዋል፡፡ ዛሬ የምናከብረው 60 ዓመታት የቆየ ተስፋ፣ 60 ዓመታት የተከፈለ መስዋዕትነት፣ 60 ዓመታት የተጻፈ ታሪክ፣ እና 60 ዓመታት ለቀጣዩ ትውልድ የተሸከምነው አደራ ነው ብለዋል። ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በስፋት መጠቀም፣ የአካባቢውን ማህበረሰብ ዋና ተጠቃሚና ባለቤት ማድረግ፣ ከአጋር ተቋማት ጋር ያለንን ትብብር ማጠናከር፣ ሳይንሳዊ ጥናትና ምርምሮችን ማጎልበት የወደፊት የጥበቃ ስራዎቻችን መሰረታዊ አቅጣጫዎች መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡
በክልሉ የአየር ንብረት ለውጥን በዘላቂነት ለመቋቋም የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ተጠናክሮ ቀጥሏል
Jul 21, 2026 97
ባህር ዳር ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፦በአማራ ክልል የአየር ንብረት ለውጥን በዘላቂነት ለመቋቋም የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብርን ተግባራዊ የማድረግ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ለግብርና ልማት ምርታማነትና የአየር ጸባይ ለውጥን መከላከል ሰፊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። በመሆኑም በክረምቱ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከ1 ሚሊዮን በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች እየተሳተፉ እንደሚገኙ ነው ያመለከቱት። በአሁኑ ወቅትም በበጋው ወቅት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በተከናወኑባቸው ቦታዎችና ሌሎች አካባቢዎች ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኖች እየተተከሉ መሆኑን ተናግረዋል።   የችግኝ ተከላ ስራው የአየር ንብረት ለውጥን ከመቋቋም ባለፈ የአርሶ አደሩን የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት ከማሳደግ አንፃር የተገኘውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል ያግዛል ብለዋል። ህብረተሰቡን በማሳተፍ እየተካሄደ በሚገኘውን የችግኝ ተከላ ከማሳካት ጎን ለጎን ተገቢውን ጥበቃና እንክብካቤ በማድረግ የጽድቀት መጠኑን ለማሳደግ እንደሚሰራም አብራርተዋል። በአዊ ዞን ጓንጓ ወረዳ አንጓይ ቀበሌ አርሶ አደር ስሜነህ አያል እንደገለጹት፣ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሩ ለእንስሳት ግጦሽ መስፋፋትና ለመኖ ልማት ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ።   በወተት ልማት፣ በንብ ማነብና በከብት ማድለብ ስራ ያረጋገጡትን ተጠቃሚነት ለማሳደግም በችግኝ ተከላ ስራ እየተሳተፉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በዚሁ ወረዳ የብዝራካኒ ቀበሌ አርሶ አደር መኮንን ፈንታው፣ የችግኝ ተከላ የአፈር ለምነትን በመጨመር ለግጦሽ መሬት ልማት እንዳገዛቸው አስረድተዋል።
በዞኑ ፍራፍሬን በኩታ ገጠም በማልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ ናቸው
Jul 20, 2026 715
ጎንደር ፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦በማእከላዊ ጎንደር ዞን ፍራፍሬን በኩታ ገጠም በማልማት የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆናቸውን የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ ገለጹ። በዞኑ በላይ አርማጭሆ ወረዳ በሹመራ ቀበሌ የቡናና አቮካዶ ፍራፍሬን በኩታ ገጠም ለማልማት የሚያስችል የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር ዛሬ ተካሂዷል።   የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በዞኑ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት የተሰጠው ትኩረት አበረታች ውጤት ለማስመዝገብ አስችሏል። ባለፉት ዓመታት በተካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር 4 ሺህ 900 ሔክታር መሬት በቡና በማልማት የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አስችሏል ነው ያሉት። በያዝነው ክረምትም በ500 ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝ እንደሚተከል ጠቁመው ከዚህ ውስጥ 100 ሄክታር የሚሆነው በላይ አርማጭሆ ወረዳ በኩታ ገጠም የሚለማ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም አርሶ አደሩን ከሰብል ልማቱ ጎን ለጎን በፍራፍሬ ልማት በማሳተፍ በዘላቂነት ሀብት ለማፍራት የሚያስችለው መሆኑን አስገንዝበዋል።   በዞኑ የላይ አርማጭሆ ወረዳ የሹመራ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ባንቺ ደመቀ ፤ ቀደም ሲል ከተከሉት የቡና ችግኝ ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ተናግረዋል። ይህንኑ ተግባር በማጠናከርም ዘንድሮ በኩታ ገጠም የቡና ችግኝ ተከላ መጀመራቸውን ነው የተናገሩት። በቡና ክላስተር ልማት እየተሳተፉ የሚገኙት አርሶ አደር ወርቁ ተፈራ በበኩላቸው፤ ቀደም ሲል የማንጎ ችግኞችን በማልማት ተጨማሪ ሃብት ለመፍጠር እንዳስቻላቸው ገልጸዋል።   አሁን ላይም ቡናን በኩታ ገጠም ለማልማት ከአጎራባች አርሶ አደሮች ጋር በመተባበር እየሰሩ መሆናቸውን አስገንዝበዋል። የፍራፍሬ ችግኞቹንም በማረም፣ በመኮትኮትና በመጠበቅ ለፍሬ ለማብቃት ትኩረት ሰጥተው እንደሚሰሩ ተናግረዋል። በዞኑ በክረምት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 141 ሚሊዮን የደን፣ የፍራፍሬና የውበት ችግኞችን የመትከል ስራ መቀጠሉን ከዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ከመቋቋም ባለፈ የወጣቶችን የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ባህል አሳድጓል
Jul 18, 2026 716
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 11/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ከመቋቋም ባለፈ የወጣቶችን የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ባህል እያሳደገ መሆኑን የአዲስ አበባ ወጣቶች ማህበር ገለጸ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃግብር የደን መመናመንና የአፈር መሸርሸርን በመከላከል በኩል አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል።   ባለፉት ዓመታት ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞች የተተከሉ ሲሆን በዘንድሮው ዓመትም 'ተስፋን እንትከል' በሚል መሪ ሐሳብ ከ8 ቢሊየን በላይ ችግኞችን ለመትከል ወደ ትግበራ ተገብቷል፡፡ መርሃግብሩ የሀገሪቱን የደንና የአረንጓዴ ሽፋን ከማሳደጉ ባለፈ ለበርካታ ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠር አስችሏል። የአዲስ አበባ ወጣቶች ማህበር ከከተማ አስተዳደሩ የከተማ ውበት እና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ጋር በመተባበር የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር በዛሬው ዕለት አካሂዷል። በመርሃ-ግብሩ የተሳተፉ ኃላፊዎችና ወጣቶች የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የአየር ንብረት ለውጥን ከመከላከል ባለፈ፣ የበጎ ፍቃድ አገልግሎት ባህልን ለማሳደግ አስተዋፅኦ እያበረከተ መሆኑን ገልፀዋል። የአዲስ አበባ ወጣቶች ማህበር ምክትል ፕሬዚዳንት ፎሊ ንጉሴ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም፣ የከተማዋን ውበት ለመጠበቅና ምቹ አካባቢን ለመፍጠር አስተዋፅኦ እንዳለው ተናግራለች። ችግኝ ከመትከል ባለፈ በዘላቂነት መንከባከብና መጠበቅ እንደሚገባም ገልፃለች። የማህበሩ ዋና ጸሐፊ ኤርሚያስ ወንድሙ በበኩሉ፣ የዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከተበሰረበት ጊዜ አንስቶ ወጣቱ በንቃት እየተሳተፈ እንደሚገኝ ተናግሯል።   መርሃ-ግብሩ ለተተኪው ትውልድ የተሻለች፣ በልምላሜና በተስፋ የተሞላች ሀገር ማስረከብ የሚያስችል መሆኑንም ገልጿል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ከተማዋን አረንጓዴ፣ ፅዱና ምቹ ስነ-ምህዳር እንድትላበስ አስችሏል ያሉት ደግሞ የቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ አንድ የጽዳትና ውበት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ የኑስ መሐመድ ናቸው።   በመርሃግብሩ የተሳተፉት ወጣት ከተማ ባልቻና ወጣት ተገኑ ቦነ በበኩላቸው ዛሬ ችግኞችን መንከባከብ ለመጪው ትውልድ ዐሻራን ማኖር በመሆኑ ችግኞችን በዘላቂነት እንደሚንከባከቡ ተናግረዋል።  
የጭስ አልባ ትራንስፖርት ዘርፍን ለማስፋፋት ከዓለም ባንክ ጋር በአጋርነት ለመሥራት ተስማምተናል-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 17, 2026 437
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 10/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ከተማን የትራንስፖርት አገልግሎት ይበልጥ ለማሻሻል ከዓለም ባንክ ጋር በጋራ ለመሥራት የሚያስችል ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች በዓለም ባንክ የኢትዮጵያ፣ ኤርትራ፣ ሱዳን እና ደቡብ ሱዳን ዳይሬክተር ከሆኑት ማርያም ሳሊም ጋር ባደረጉት ውይይት፣ ከተማ አስተዳደሩ የትራንስፖርት ዘርፉን ለማዘመን እና በተለይም የጭስ አልባ ትራንስፖርት (E-mobility) ተደራሽነትን በስፋት ለማዳረስ እያከናወነ ባለው ሥራ ዙሪያ በዝርዝር መምከራቸውን ገልጸዋል።   በውይይታቸውም አስተዳደሩ የጀመራቸውን ሥራዎች ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ ውይይት ማድረጋቸውን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ጠቁመዋል። እንዲሁም በዘርፉ የተሰማሩ የግል ተቋማትን ለመደገፍ ከዓለም ባንክ ጋር በአጋርነት እና በትብብር በጋራ ለመሥራት ተግባብተናል ብለዋል።   ከንቲባ አዳነች ለዳይሬክተሯ ማርያም ሳሊም እና አብረዋቸው ለነበሩት የቴክኒካል ቡድን አባላት በራሳቸው እና በአዲስ አበባ ሕዝብ ስም የላቀ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
በምዕራብ ሸዋ ዞን በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከ8 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በፍራፍሬ እየለማ ነው
Jul 16, 2026 518
አምቦ፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦በምዕራብ ሸዋ ዞን በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር 8 ሺህ 463 ሄክታር መሬት የሚሸፍን የፍራፍሬ ልማት እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በምዕራብ ሸዋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት የደን ልማት ባለሙያ አቶ ጉደታ ጡር ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በተያዘው ክረምት ከ15 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የፍራፍሬ ችግኞች ተዘጋጅተው እየተተከሉ ይገኛሉ።   የሚተከሉት የፍራፍሬ ችግኞች በአካባቢው የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ማኅበረሰቡ ተጨማሪ ገቢ በማግኘት የኢኮኖሚ ተጠቃሚነቱን እንዲያሳድግ ጉልህ ሚና እንደሚኖራቸውም ገልጸዋል። በመርሐ ግብሩ ከተዘጋጁት የፍራፍሬ ዝርያዎች መካከል ፓፓያ፣ አቮካዶ፣ ሙዝ እና አፕል እንደሚገኙበትም ባለሙያው ጠቁመዋል። በልማት ሥራው ዙሪያ ለአርሶ አደሮቹ ሥልጠና መሰጠቱን የጠቀሱት አቶ ጉደታ፤ በአሁኑ ወቅትም አስፈላጊው ሙያዊ ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው እንደሚገኝ አስረድተዋል። በዞኑ በክረምቱ ወቅት በአጠቃላይ በ8 ሺህ 463 ሄክታር መሬት ላይ የፍራፍሬ ችግኝ ተከላ እየተካሄደ መሆኑንና በዚህ የልማት ሥራ ላይ 131 ሺህ 576 አርሶ አደሮች በመሳተፍ ላይ እንደሚገኙም አስታውቀዋል።   በዞኑ የሚገኙ አርሶ አደሮች ከመደበኛ የግብርና ሥራቸው በተጓዳኝ በፍራፍሬ ልማት ላይ በመሰማራታቸው ተጨማሪ ገቢ ማግኘት መቻላቸውን ጠቅሰዋል። ከዚህም በተጨማሪ ባለፉት ዓመታት የተተከሉ የፍራፍሬ ችግኞች የአፈር መሸርሸርን ለመከላከልና የደረቁ ምንጮች እንዲያንሰራሩ በማድረጋቸው፣ የአርሶ አደሮቹን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን አክለዋል። በምዕራብ ሸዋ ዞን በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር እስካሁን ከ11 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በፍራፍሬ ልማት መሸፈኑን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር አሳይታለች
Jul 16, 2026 470
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 9 /2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ፅኑ ቁርጠኝነት በተግባር ማሳየቷን የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ፀጋ ገለጹ። በኢትዮጵያ የአረንጓዴ አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን ማጠናከር ላይ ለተቀረጸው የምርምር ፕሮጀክት የተዘጋጀ የማስጀመሪያ አውደ ጥናት እየተካሄደ ይገኛል።   በአውደ ጥናቱ መክፈቻ ላይ የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ፀጋ እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ በመቅረጽ፣ ለአረንጓዴ ልማት ያላትን ፅኑ ቁርጠኝነት በተግባር አሳይታለች። ይህም በታዳሽ ኃይል መስፋፋት፣ በዘላቂ ግብርና እና ለአካባቢ ጥበቃ ተስማሚ በሆኑ የኢንዱስትሪ እንቅስቃሴዎች ውስጥ በግልጽ ይንጸባረቃል ብለዋል። አረንጓዴ ኢኮኖሚን መገንባት የመንግሥትን ጥረት ብቻ ሳይሆን የሁሉንም አካላት ንቁ ተሳትፎ እንደሚጠይቅም አንስተዋል። በተለይም አነስተኛና መካከለኛ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን ማሳተፍ ወሳኝና አማራጭ የሌለው ተግባር መሆኑን ገልጸው፤ እነዚህ ኢንተርፕራይዞች ለኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለእሴት ሰንሰለት ዕድገት፣ ለሀገር ውስጥ ምርት እንዲሁም ለኢኮኖሚ ብዝኃነት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አስገንዝበዋል። እነዚህ ኢንተርፕራይዞች ለኢትዮጵያ የኢንዱስትሪ ሽግግር፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ለእሴት ሰንሰለት ዕድገት፣ ለሀገር ውስጥ ምርት እንዲሁም ለኢኮኖሚ ብዝኃነት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አስገንዝበዋል። ወደ አረንጓዴ ማኑፋክቸሪንግ የሚደረገው ሽግግር የመንግስት፣ የግልና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የተቀናጀ አካሄድ ያስፈልጋል ብለዋል። በኢንስቲትዩቱ በአምራች ዘርፍ የማዕድን ዘርፍ ክፍል ኃላፊ እና መሪ ተመራማሪ ነጻነት ጆቴ (ዶ/ር)፤ በዓለም አቀፍ ደረጃ አካባቢን የማይበክልና ዘላቂ የምርት ሥርዓት መገንባት አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል።   በኢትዮጵያ የሚገኙ የአረንጓዴ ማኑፋክቸሪንግ ኢንተርፕራይዞችን የሚዳስስ ጥናት እንደሚደረግ ነው የገለጹት። የጥናቱ ዋና ዓላማ የኢንተርፕራይዞቹን ወቅታዊ ሁኔታ፣ ዕድሎችና ፈተናዎች በማመላከት ተወዳዳሪነታቸውን ማሳደግ ነው ብለዋል። በአፍሪካ ክላይሜት ፋውንዴሽን የፕሮጀክት ማናጀር ሳህሌ ታምሩ፤ ፋውንዴሽኑ በታዳሽ ኃይል፣ አረንጓዴ ኢንዱስትሪ፣ የትራንስፖርትና የፋይናንስ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ጥናቶችና ምርምሮችን እየደገፈ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።   ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዘርፍ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም በዓለም አቀፍ ገበያ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ተወዳዳሪነቷንና ተጠቃሚነቷን ለማሳደግ ጥናቱ አስተዋጽኦ የሚያደርግ በመሆኑ በጋራ እንሰራለን ብለዋል።
የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖዎችን ለመቋቋም የተገቡ ቃሎች ወደ ተጨባጭ ተግባር መቀየር አለባቸው
Jul 15, 2026 1401
አዲስ አበባ ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ) ፦ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትላቸውን አሉታዊ ተፅዕኖዎች ለመቋቋም የተገቡ ቃሎችን ወደ ተጨባጭ ተግባር መቀየር አስፈላጊ ነው ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዎን ጢሞቴዎስ ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የኮፕ 32 ፕሬዚዳንት ዶክተር ጌዲዎን ጢሞቴዎስ ዛሬ ከኮፕ 21 ፕሬዚዳንት ከሆኑት ሎረን ፋቢየስ ጋር ተወያይተዋል። ‎ ‎በውይይቱም ሎረን ፋቢየስ በዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ላይ ታላቅ ስኬት የተመዘገበበትን የፓሪስ ስምምነት በማጽደቅ የተጠናቀቀውን ኮፕ 21ን የመሩበትን ልምድ አካፍለዋል። ‎በተጨማሪም ለኮፕ 32 በሚደረጉ ዝግጅቶች እንዲሁም ስኬታማ የኮፕ 32 ጉባኤን ለማካሄድ አስተዋጽኦ ሊኖራቸው በሚችሉ ጉዳዮችና ካለፉት የኮፕ ጉባኤዎች በተገኙ ትምህርቶችና ግንዛቤዎች ላይ የሁለቱ መሪዎች ውይይት ትኩረት አድርጓል። ‎ ‎የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዎን ጢሞቴዎስ(ዶ/ር) የፓሪሱ ስምምነት ለዓለም አቀፍ የአየር ንብረት እርምጃዎች ያለውን ዘላቂ ጠቀሜታ ገልጸው፣ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትላቸውን አሉታዊ ተፅዕኖዎች ለመቋቋም የተገቡ ቃሎችን ወደ ተጨባጭ ተግባር የመቀየርን አስፈላጊነት አፅንዖት ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ በባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ ላይ እምነትን የሚያጠናክር፣ ግልጽ፣ አካታች እና በአባል ሀገራት የሚመራ የኮፕ 32 ሂደትን ለመተግበር ያላትን ቁርጠኝነትም በድጋሚ አረጋግጠዋል። ሚኒስትሩ አክለውም በይዘትና ድርድር፣ በሎጂስቲክስና ኦፕሬሽን፣ በአጋርነት እንዲሁም ሚዲያና ኮሙኒኬሽንን ጨምሮ በተለያዩ ዘርፎች በዝግጅት ረገድ የተመዘገቡት ተጨባጭ እድገቶችን አሳይተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም