አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
አረንጓዴ ዐሻራ የትውልዱ ዳግማዊ ዓድዋ የኢትዮጵያ የማንሰራራት ምልክት
Sep 7, 2026 176
አረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ መትከል ብቻ አይደለም፤ አካባቢን ለኑሮ ምቹና ማራኪ ገጽታ ማላበስ፣ የተፈጥሮን ሥነ-ምህዳር መጠበቅ፣ ለዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ መቋቋም ጠጠር መጣል፣ ኢትዮጵያ የዓለም ነባራዊ ሁኔታ የሚገዳትና ለመፍትሔውም በግንባር ቀደምትነት የምትሳተፍ መሆኗን ማሳያ ጭምር እንጂ። አረንጓዴ ዐሻራ ለኢትዮጵያ ወንዞቿን በደለል ከመሞላት፣ አፈሯን ከመሸርሸር መታደግ፣ የዜጎቿን የምግብ ዋስትና የማረጋገጥና ምድሯን አረንጓዴ የማልበስ ኢኒሼቲቭ ነው። ከሰባት ዓመት በፊት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ኢኒሼቲቭ ሲያስጀምሩ፤ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋም አይበገሬ ኢኮኖሚ መገንባት የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥ አንዱ ሰበዝ እንደሆነ በመናገር ነበር። ኢትዮጵያ ዛሬ ለምግብነትና ለደን ልማት አገልግሎት፣ ለአካባቢ ውበትና መናፈሻ የሚውሉ በርካታ ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል ታሪክ ሠርታለች። በአረንጓዴ ዐሻራ የደረቁ ሐይቆች አገግመዋል፤ በደለል የሚሞሉ ሐይቆችን መታደግ ተችሏል፤ የሚሸረሸረው ለም አፈርም ከመታጠብ ድኗል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አረንጓዴ ዐሻራ የተረጅነት ታሪክን በአዲስ ምዕራፍ በመተካት የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትን የማረጋገጥ ጉዞ ጅማሬ መሆኑን ገልጸዋል። አረንጓዴ ዐሻራ ዜጎች በአካባቢያቸው የተመጣጠነ ምግብ እንዲያገኙ በማስቻል ለኢኮኖሚ ማንሰራራት መሠረት እየጣለ መጥቷል ብለዋል። አረንጓዴ ዐሻራ ከኢትዮጵያ ሉዓላዊነትና ብልፅግና ጋር በቀጥታ የተሳሰረ ሀገራዊ ትልም ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የትውልዱ ዳግማዊ ዓድዋና የኢትዮጵያ የማንሰራራት ምልክት መሆኑን ገልጸዋል። ትውልዱ እንደ ትናንቱ ዓድዋ ሁሉ የዛሬውን አረንጓዴ ዐሻራ ከአባቶቹ የወረሰው የሀገር ማስቀጠያ ስንቅ በማድረግ በታሪክ ያወሳዋል ብለዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)፤ የአረንጓዴ ዐሻራ ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያላትን መሪነትና የተለየ ሚና የሚያጎላ የድል ችቦ መሆኑን ገልጸዋል። በአረንጓዴ ዐሻራ የተመዘገበው ውጤት በአፍሪካ አህጉር የወካይነት ሚና እንዲኖራት ማስቻሉን በማንሳት፤ ዓለም አቀፋዊና አህጉራዊ ኩነቶችን ለማስተናገድ እምነት የሚጣልባት ሀገር ሆናለች ብለዋል። ይህም ኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃና በአየር ንብረት ዲፕሎማሲ በዓለም አቀፍ ደረጃ በግንባር ቀደምትነት እንድትሰለፍ ማድረጉን ገልጸዋል። የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ፤ የአረንጓዴ ዐሻራ በአካባቢ ጥበቃ ብቻ የተገደበ ሳይሆን ለግብርና ምርትና ምርታማነት ገንቢ ሚና አለው ብለዋል። በኢትዮጵያ የሰብል ምርት ዕምርታዊ ለውጥ እንዲያስመዘግብ በማስቻል በስንዴ ምርት ብቻ ከተረጂነት ወደ ትርፍ አምራችነት በመሸጋገር የኢትዮጵያ የማንሰራራት ጉዞ እያበሰረ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአቮካዶና በሌሎች የሆርቲካልቸር ምርቶች ከሀገር ውስጥ ፍጆታ ባለፈ ለውጭ ገበያ በማቅረብ ከፍተኛ መጠን ያለው የውጭ ምንዛሪ እንድታገኝ አስችሏታል ብለዋል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርና ሌሎች የተቀናጁ የተፋሰስ ጥበቃ ሥራዎች በውሃ ሀብት ልማት በኩል ጉልህ ለውጥ ማስገኘታቸውን ገልጸዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ የሐይቆችን የደለል ክምችት በመቀነስ ብዙ ውሃ እንዲይዙ በማድረግ የግድቦችን ዕድሜ ማራዘም አስችሏል ብለዋል። የደረቁ ምንጮችና ሐይቆች እንዲያገግሙ አድርጓል ያሉት ሚኒስትሩ፤ የውሃና የተፈጥሮ ሀብትን ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ ማስቻሉን ገልጸዋል።
ጽዱ ኢትዮጵያን ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ በርካታ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Sep 7, 2026 79
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ):- ጽዱ ኢትዮጵያን ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ በርካታ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የፌዴራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ ገለጹ። «ፅዱ ኢትዮጵያ ለትውልድ» በተሰኘው ሀገር አቀፍ ንቅናቄ ማዕቀፍ የተዘጋጀና በአደገኛ ቆሻሻ አስተዳደር፣ በኤሌክትሮኒክስ ብክነት (e-waste) እንዲሁም በኬሚካሎች ደህንነቱ የተጠበቀ አያያዝና ማስወገድ ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ የፌዴራልና የክልል አካባቢ ጥበቃ ተቋማት ኃላፊዎች፣ የጤና ቢሮዎች ተወካዮች፣ የምርምርና የአካዳሚክ ተቋማት ተመራማሪዎች እንዲሁም በግል ዘርፍ የሚንቀሳቀሱ የቆሻሻ አስተዳደር ኦፕሬተሮች ተገኝተዋል። የፌዴራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ በወቅቱ እንደገለጹት፤ በሀገሪቱ «ጽዱ ኢትዮጵያን» በመፍጠር በኩል በርካታ አርዓያነት ያላቸው ተግባራት እየተከናወኑ ነው፡፡ በዚህም የህብረተሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ በከፍተኛ ሁኔታ መቻሉንና ለአካባቢ ጥበቃና ጽዳት ጥሩ ውጤት እየተገኘ መሆኑን አመልክተዋል። በቀጣይም የሚሰራውን ስራ በማጠናከር ጽዱ ኢትዮጵያን ለትውልድ ማስተላለፍ እንደሚገባ አመልክተዋል። ከዚህ ጋር በተያያዘም በአካባቢ ላይ ጉዳት የሚያደርሱ አገልግሎት የጨረሱ ኤሌክትሮኒክስ ቁሳቁሶችና ሌሎች ቆሻሻዎችን ለመከላከል በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ መንግስት ችግሩን ለመከላከል የሕግ ማዕቀፎችን፣ ደረጃዎችንና የሕግ ማስፈጸሚያ ሥርዓቶችን በማጠናከር በኩል የሚጠበቅበትን ሚና እየተወጣ መሆኑንም ምክትል ዳይሬክተሯ አስታውቀዋል። በመሆኑም ችግሩን ይበልጥ ለመቅረፍ የሁሉም ርብርብ ወሳኝ መሆኑንና የመንግሥት፣ የግሉ ዘርፍ፣ የምርምር ተቋማትና የሕብረተሰቡ ቅንጅታዊ አሠራር ይበልጥ መጠናከር እንዳለበት ጠቁመዋል። በአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የአካባቢ ተከባሪነትና ተፈጻሚነት መሪ ሥራ አስፈጻሚ አዲሱ ጥበቡ በበኩላቸው አደገኛ ቆሻሻ ዓለም አቀፍ ትኩረት የተሰጠው ችግር መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያም የችግሩን አሳሳቢነት በመረዳት ቆሻሻዎችን መከላከልና መቆጣጠር የሚያስችል ሥርዓት ዘርግታ እየሰራች ትገኛለች ብለዋል። የፒዩር ኧርዝ የቴክኒካል ፕሮግራሚንግ ዳይሬክተር በረከት ተስፋዬ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃ ከፍተኛ ትኩረት ሰጥታ ውጤታማ ተግባራት እያከናወነች መሆኑን ገልጸዋል። ድርጅታቸው ከመንግሥት ጋር የተቀናጀ አሠራር ዘርግቶ እየሰራ መሆኑንና በቀጣይም ይህ የጋራ ትብብር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ መፍትሔ በመቀየስ ረገድ መሪ ሚና መጫወት ይገባታል-ክላቨር ጋቴቴ
Sep 7, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 2/2018 (ኢዜአ)፦ አፍሪካ በዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ ድርድሮችና መፍትሔዎች ላይ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ የጎላ ሚና መጫወት እንዳለባት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክላቨር ጋቴቴ ገለጹ፡፡ 14ኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ እና ልማት ጉባኤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። ጉባኤው "ከተስፋ ቃል ወደ ተግባር፤ የቤሌም-አንታልያ-አዲስ አበባ ፍኖተ ካርታ" በሚል መሪ ሐሳብ ነው እየተካሄደ ያለው። የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክላቨር ጋቴቴ በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፣ አፍሪካ ለዓለም አቀፍ የካርቦን ልቀት የምታበረክተው አስተዋጽኦ አራት በመቶ ቢሆንም የችግሩን ከባድ መዘዝ እየተሸከመች ትገኛለች። ሆኖም ይህ እውነታ ለአፍሪካ የተጎጂነት ታሪክ ብቻ ሆኖ ሊቀጥል እንደማይገባ ተናግረው አፍሪካ ያላትን ከፍተኛ የታዳሽ ኃይል አቅም፣ የማዕድን ሀብቶች፣ ወጣት የሰው ኃይል እና እያደገ ያለውን ገበያ በመጠቀም በዓለም አቀፍ ደረጃ መፍትሔዎችን በመቀየስ ረገድ መሪ ሚና መጫወት እንዳለባት ገልጸዋል። አፍሪካ እስከ እ.ኤ.አ 2030 ድረስ የተቀመጡ የአየር ንብረት ግቦችን ለመተግበር በየዓመቱ 277 ቢሊዮን ዶላር የሚያስፈልጋት ቢሆንም እያገኘች ያለችው ከፍላጎቷ 11 በመቶ ያህሉን ብቻ ነው ብለዋል። የአየር ንብረት እርምጃዎች ከኃይል ተደራሽነት፣ከኢንዱስትሪ ልማት እና ከሥራ እድል ፈጠራ ጋር ተያይዘው መከናወን እንዳለባቸው አሳስበዋል። ከ600 ሚሊዮን በላይ አፍሪካውያን አሁንም የኤሌክትሪክ አገልግሎት ያላገኙ በመሆናቸው የታዳሽ ኃይልን ማስፋፋት የኢኮኖሚው መሠረት ሊሆን ይገባል ብለዋል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣናን በመጠቀም በሀገር ውስጥ የሚመረቱ ሀብቶች ላይ እሴት በመጨመር አህጉራዊ የእሴት ሰንሰለት መገንባት ይቻላል ሲሉም ገልጸዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ስኬቶችን በማላቅ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቷል- ከንቲባ ከድር ጁሃር
Sep 6, 2026 159
ድሬዳዋ፣ ጳጉሜን 1/2018 (ኢዜአ)፡- የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ስኬቶችን በማላቅ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና የአየር ንብረት ለውጥ ሚዛንን ለመጠበቅ ትኩረት መሰጠቱን የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ተናገሩ። የእምርታ ቀን በአረንጓዴ አሻራ ችግኝ በመትከልና እና በሌሎች ዝግጅቶች በድሬዳዋ እየተከበረ ነው። "እምርታ ለኢትዮጵያ ከፍታ" በሚል መሪ ሃሳብ በክቡር ዶክተር አርቲስት አሊ ቢራ ፓርክ የችግኝ ተከላ መርሀግብር ተካሂዷል። ከንቲባ ከድር ጁሃር በወቅቱ እንደተናገሩት፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታዎችን በማላቅ ለምግብ ዋስትና መረጋገጥና የአየር ሚዛን ለመጠበቅ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። የመደመር መንግስት ባለፉት ዓመታት ተግባራዊ ካደረጋቸው እና የአገር የከፍታ ጉዞ ዕውን ከሆኑባቸው ተግባራት መካከል አንዱ የአረንጓዴ አሻራ መሆኑን አንስተዋል። በድሬዳዋ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብሮች ችግኞች የአካባቢውን ስነምህዳር በመለወጥ፣ የከርሰ ምድር ውሃ እንዲጨምር በማገዝና የተመናመነውን ደን በመመለስ ወሳኝ ሚና ማበርከታቸውን አስታውቀዋል። በተለይ በድሬዳዋ ሲከሰት የነበረን የጎርፍ አደጋን በላቀ ደረጃ በመቀነስና ውሃን ወደ ጥቅም ለመለወጥ እያበረከተ ያለው አስተዋፅኦ ለማስቀጠል ችግኞች በላቀ ህዝባዊ ተሳትፎ እየተተከሉ ይገኛሉ ብለዋል። ዛሬም በእምርታ ቀን በህዝብ እና በአመራሩ ተሳትፎ የተተከሉት ችግኞች የተገኘውን እመርታ ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ እንዳላቸው አንስተዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኑረዲን አብደላ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የእምርታ ቀን በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የተገኙ ውጤቶችን በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል መደላድል የተፈጠረበት ነው። በተለይ መርሀግብሩ የከርሰ ምድርና የገጸ ምድር ውሀ ሀብት እንዲያድግ መሰረት በመጣሉ የገጠሩ ህብረተሰብ አነስተኛ መስኖ በመጠቀም ምርትና ምርታማነትን በመጨመር ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር እያገዘ ይገኛል ብለዋል። የእምርታ ቀንን ምክንያት በማድረግ ዛሬ በተካሄደው የችግኝ ተከላ መርሀግብር ላይ የአስተዳደሩ ከፍተኛ አመራሮች እና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳታፊ ሆነዋል።
አረንጓዴ አሻራ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን በመከላከል ቁልፍ ሚና እየተጫወተ ነው - የአፍሪካ ህብረት
Sep 5, 2026 238
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 30/2018 (ኢዜአ)፡- የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖዎችን ለመመከትና ለብዝሃ ህይወት ጥበቃ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ የአፍሪካ ህብረት የዘላቂ ከባቢና ብሉ ኢኮኖሚ ዳይሬክተር ሃርሰን ንያምቤ ገለጹ። ዳይሬክተሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ አረንጓዴ አሻራ ንጹህ አየርን ጨምሮ ሌሎች ስነ-ምህዳራዊ ጥቅሞችን ከማስገኘቱም በላይ፣ የካርበን ልቀትን በመቀነስ የአየር ሙቀት መጨመርን ለመከላከል እንደሚያስችል ተናግረዋል። የተራቆተ መሬትንና የአካባቢ ስነ ምህዳር እንዲያገግም በማድረግ የአየር ንብረት ለውጥ ጉዳትን ለመከላከል እየተደረገ ባለው ጥረት ውስጥ ወሳኝ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በጥቅሉ ሲታይ የአረንጓዴ አሻራ በርካታ ሁለገብ ጥቅሞች ያሉት ሀገራዊ ኢኒሼቲቭ መሆኑንም አንስተዋል። የአፍሪካ ሀገራት በአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ተግባራት ላይ የልምድ ልውውጥ ማድረግ እንደሚገባቸው የገለጹት ዳይሬክተሩ፤ በዚህ ረገድም በአካባቢ ጥበቃ ላሉባቸው ተግዳሮቶች መፍትሄ ለማበጀት ከኢትዮጵያ ተሞክሮ መውሰድ እንደሚችሉ ነው የገለጹት። ኢትዮጵያም ስኬታማ ተሞክሮዎቿን ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በማካፈል ግንባር ቀደም ሚና መጫወት እንዳለባት ዳይሬክተሩ አንስተዋል።
የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ልምድ ለማካፈል ወጣቶች ወደተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ሊያቀኑ ነው
Sep 2, 2026 467
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ልምድ ለማካፈል ወጣቶች ወደተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ሊያቀኑ መሆኑ የብልፅግና ፓርቲ ወጣቶች ክንፍ ምክትል ፕሬዝዳንትና የዋና ጽህፈት ቤት ሀላፊ አባንግ ኩመዳን ገለጹ። ከመላው የሀገሪቱ የተውጣጣ የወጣቶች ቡድን በሦስት የአፍሪካ ሀገራት ነገ የሚጓዝ ይሆናል። የብልፅግና ፓርቲ ወጣቶች ክንፍ ምክትል ፕሬዝዳንት እና የዋና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አባንግ ኩመዳን እንደገለጹት፤ ወጣቶቹ የሚጓዙት ጋና፣ ዚምባብዌና ናይጄሪያ ነው። በዚህ የጉዞ መረሃ ግብር ሀያ አራት ወጣቶች የሚሳተፉ ሲሆን፤ የተለያዩ ዝርያ ያላቸው ችግኞችን በመትከል ልምድ እንደሚያካፍሉም አስታውቀዋል። መርሃ ግብሩ ለሁለተኛ ጊዜ የሚካሄድ መሆኑን ገልጸው፤ ከዚህ ቀደም የብልጽግና ወጣት ክንፍ በፓኪስታን የችግኝ ተከላ ማካሔዳቸውን ገልጸዋል። የልዑካኑ ጉዞ የልምድ ልውውጥ ከማድረግ በተጨማሪ ወንድማማችነትን ለማጠናከር የሚያግዙ ተግባራትን እንደሚያከናውን አስታውቀዋል። በቀጣይም ወጣቶች ወደ ተለያዩ ሀገራት በመሄድ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በማከናወን የኢትዮጵያን ልምድ የማካፈል ተግባርን ያጠናክራል ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተጀመረው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በስኬታማነት እየተከናወነ ይገኛል። በዚህ ዓመት ብቻ ከ800 ሚሊዮን በላይ ችግኞች በአንድ ጀምበር መተከላቸው ይታወሳል። ይህ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ዓለም አቀፍ እውቅና እያገኘ ሲሆን የተለያዩ ሀገራትም ተሞክሮውን እየወሰዱት ይገኛሉ።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት ምዕራብ፣ ሰሜን ምዕራብ፣ደቡብ ምዕራብና መካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ይኖራቸዋል
Sep 2, 2026 797
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ) ፦ በሚቀጥሉት አስር ቀናት ምዕራብ፣ሰሜን ምዕራብ፣ደቡብ ምዕራብ እና መካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖራቸው የኢትዮጵያ የሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ከነሃሴ 26 ቀን ጀምሮ እስከ ጳጉሜን አምስት ቀን 2018ዓ.ም ድረስ በኢትዮጵያ የሚኖረውን የአየር ፀባይ ሁኔታ በተመለከተ ለኢዜአ መግለጫ ልኳል። በመግለጫውም ነሀሴ ወር የክረምት የመጨረሻ ወቅት በመሆኑ በሰሜን ምሥራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች የዝናብ መጠን እንደሚቀንስ በማመላከት ለረጅም ጊዜ ደረቅ ሆነው የሰነበቱት ደቡብና ደቡብ ምሥራቅ አካባቢዎች ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸውን እንደሚያስተናግዱ ጠቁሟል። በምሥራቅ፣ በሰሜን ምሥራቅና በመካከለኛው ኢትዮጵያ አካባቢዎች የዝናብ መጠንና ስርጭት እንደሚቀነስ ነገር ግን በደቡብና ደቡብ ምሥራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች በስርጭትም በመጠንም የተሻለ ዝናብ እንደሚያገኙ በመግለጫው ተመላክቷል። በሚቀጥሉት አስር ቀናትም ምዕራብ፣ሰሜን ምዕራብ፣ደቡብ ምዕራብ እና መካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖራቸው ይጠበቃል። ማኅበረሰቡም ከላይ በተጠቀሱት ቦታዎች ላይ የሚኖረውን የእርጥበት ሁኔታ ታሳቢ ባደረገ መልኩ የግብርና ስራቹን እንዲያከናውን ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል። ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው እርጥበት ከሚያስተናግዱ ቦታዎች መካከል ቄለም ወለጋ፣ ኢሉባቦር የምዕራብ ፣መካከለኛ ፣ደቡብ እና ሰሜን ጎንደር፣ የሰሜን፣ የምዕራብ እና ምሥራቅ ጎጃም ዞኖች፣ ካማሺ፣ መተከል፣ አሶሳ ዞኖች እንደሚገኙበት ከመግለጫው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል። ሁሉም ሸዋ ዞኖች፣ አኝዋክ፣ ከፋ፣ ምዕራብ ኦሞ፣ ጉራጌ ፣አዲስ አበባ ፣ድሬዳዋ፣ የምዕራብ ፣የሰሜን ምዕራብ ፣መካከለኛው፣ ምሥራቅ እና ደቡብ ትግራይ ዞኖች ፣የሲዳማ አብዛኛው የክልሉ ዞኖች ደግሞ ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ከሚያስተናግዱ አካባቢዎች መካከል መሆናቸው ተጠቁሟል። ኢንስቲትዩቱ ቀላል፣መካከለኛ እና ከባድ እርጥበትን የሚያስተናግዱ የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ፣ የመኸር ሰብል አብቃይ ፣ አርብቶ አድርና ከፊል አርብቶ አደር አካባቢዎች የሚገኙ የማኅበረሰብ ክፍሎች ይህን የአየር ሁኔታ ለግብርና ስራዎቻቸው እንዲያውሉ አስገንዝቧል። ይህ በእንዲህ እንዳለ መካከለኛ እና ከባድ የዝናብ መጠን የሚያስተናግዱ አካባቢዎች ተደፋታማ ማሳዎች ላይ የተዘጉ የማፋሰሻና የማንጣፈፊያ ቦዮች ክፍት እንዲሆኑ ማድረግ፣ የሰብል በሽታን አረምን አስቀድሞ መከላከል ፣የአፈር መሸርሸር ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራት ማከናወን፣ እና አርሶ አደሮችም የማሳ ጉብኝት በየጊዜው በማድረግ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባም አሳስቧል። ከቀላል እስከ መካከለኛ እርጥበት የሚያገኙ ቦታዎች ደግሞ የሚገኘውን እርጥበት በአግባቡ ጥቅም ላይ ማዋል፣ የዝናብ ውሀን በማሰባሰብ በደረቅ ወቅቶች መጠቀም ፣የአፈር ውስጥ ትነትን መጠንን ለመቀነስ የሚያስችሉ ተግባራትን ማከናወን ፣የእንስሳት ግጦሽ ሳርን በአግባቡ መያዝ ተገቢ ነውም ተብሏል። ለተከታታይ አስር ቀናት የሚቆየው አየር ፀባይ ሁኔታም የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የሀገሪቱ ተፋሰሶች ላይ ከዝቅተኛ እስከ ከፍተኛ መጠን ያለው የገፀ ምድር የውሃ ፍሰት እንደሚኖራቸው ኢንስቲትዩቱ ገልጿል።
በአፍሪካ አደጋዎችን ለመቋቋም በቴክኖሎጂ የተደገፈና በትብብር ላይ የተመሰረተ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት ተግባራዊ ማድረግ ይገባል
Sep 2, 2026 592
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፦በአፍሪካ የአየር ንብረት መዛባትንና መሰል አደጋዎችን ለመቋቋም በቴክኖሎጂ የተደገፈና በትብብር ላይ የተመሰረተ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት ገቢራዊ ማድረግ እንደሚገባ የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ገለጸ። ኢትዮጵያ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓትን የብሔራዊ የልማት ዕቅዷ አካል ማድረጓም ተገልጿል። የአፍሪካ ቀጣና የቅድመ ማስጠንቀቂያ ለሁሉም ፎረም በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን መካሄድ ጀምሯል። የቅድመ ማስጠንቀቂያ ለሁሉም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሀፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዥ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2022 ይፋ የተደረገ ሲሆን እስከ 2027 እያንዳንዱን ሰው በአየር ንብረት ለውጥ መዛባትና በተፈጥሮ አደጋዎች መጠበቅ የሚያስችል ኢንሼቲቭ ነው። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ከተመድ የአደጋ ስጋት ቅነሳ ቢሮና ሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበር የአፍሪካ የተቀናጀ አይነተ ብዙ አደጋ ቅድመ ማስጠንቀቂያና ቅድመ እርምጃ ሥርዓት ተግባራዊ አድርጓል። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሀና አበበ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የአፍሪካ ቅድመ ማስጠንቀቂያ ፎረም ወቅታዊና ተገቢ ነው። አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ መዛባት ድርቅ፣ ጎርፍ እና ሌሎችን አደጋዎችን በተደጋጋሚ እያስተናገደች መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም ሴቶችና ህፃናት ጨምሮ በርካታ የማህበረሰብ ክፍሎች የአደጋው ገፈት ቀማሽ እየሆኑ ነው ብለዋል። በመሆኑም ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የውስጥ የፋይናንስ አቅምን ማጎልበትና ተቋማዊ አንድነት ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል። በአፍሪካ የአየር ንብረት መዛባትና መሰል አደጋዎችን ለመቋቋም በቴክኖሎጂ የተደገፈና በትብብር ላይ የተመሰረት የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት ተግባራዊ ማድረግ ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓትን የብሔራዊ የልማት ዕቅዷ አካል ማድረጓን ጠቅሰው፤ በሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ በቴሌኮሙኒኬሽን፣ በፋይናንስና ሌሎችም ተቋማት መካከል ጠንካራ ትብብር መፍጠር እንደሚገባ ተናግረዋል። ማንም ሀገር ብቻውን የአደጋ ስጋት ቅነሳ ስትራቴጂን ውጤታማ ማድረግ እንደማይችል ገልጸው፤ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ሀገራትና የተለያዩ አጋር አካላት ጋር በአይነተ ብዙ የቅደመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት በጋራ ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል። በአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን የዘላቂ አካባቢና ብሉ ኢኮኖሚ ዳይሬክተር ሀርሰን ኒያምቤ፤ በአፍሪካ ቀጣይነት ያለው የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓትን በማጠናከር ማህበረሰቡን አደጋን የመቋቋም አቅም መገንባትና ከአደጋ መጠበቅ ይገባል ብለዋል። የመንግሥታቱ ድርጅት እንደ አውሮፓውያን ዘመን አቆጣጠር በ2027 እያንዳንዱን ሰው ከአየር ንብረት ለውጥ መዛባትና መሰል አደጋዎች መጠበቅ የሚለውን ግብ ለማሳካት ውይይቱ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ጎርፍና የተራዘመ ደርቅ፣ በማህበረ-ኢኮኖሚ፣ እና በሌሎች አደጋዎች ተጋላጭነት ተባብሶ መቀጠሉን በመግለጽ፤ አፍሪካውያን ውስጣዊ ትብብራቸውን ማጠናከር አለባቸው ብለዋል። አደጋ ድንበር የለውም ያሉት ዳይሬክተሩ፤ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን በአይነቱ ብዙ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት የአባል ሀገራቱን አቅም ለመገንባት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ቢሮ ዳይሬክተር ኤግነስ ኪጃዚ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአፍሪካ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት የአመራር ቁርጠኝነት እያደገ በመምጣቱ መሻሻል እያመጣ መሆኑን ተናግረዋል። ይሁን እንጂ አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ መዛባትና መሰል የተፈጥሮ አደጋዎች በፍጥነትና በተወሳሰበ ሁኔታ ተባብሰው ቀጥለዋል ብለዋል። በመሆኑም ችግሩን ለመቆጣጠር የቅደመ ማስጠንቀቂያ ስርዓቱን በቴክኖሎጂ፣ በፋይናንስና በሀገራት የተቀናጀ አሰራር መምራት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። የመንግሥታቱ ድርጅት የ2027 ግብ ጠቃሚ መሰረት መሆኑን በመግለፅ፤ በአፍሪካ የፋይናንስ ተቋማት ለቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት ግንባታ ዘላቂና እምነት የሚጣልባቸው መሆን አለባቸው ብለዋል። በአፍሪካውያን መካከል ቀጣናዊ ትብብርን ማጠናከር የሚያስችሉ ተቋማትን መገንባት እንደሚገባ በመጥቀስ፤ የዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል።
የመጀመሪያው የአረንጓዴ ኢንቨስትመንት ፎረምና ኤግዚቢሽን በአዲስ አበባ ይካሄዳል - የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት
Sep 1, 2026 368
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግርና ዘላቂ የኢንቨስትመንት እድል የሚያሰፋ የመጀመሪያው የአረንጓዴ ኢንቨስትመንት ፎረምና ኤግዚቢሽን በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ የአዲስ አበባ ንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት አስታውቀ። የምክር ቤቱ ምክትል ዋና ጸሐፊ ካሳሁን ማሞ፤ ምክር ቤቱ ከኔዘርላንድ የልማት ድርጅት ጋር በመተባበር የሚያዘጋጀውን የአረንጓዴ ኢንቨስትመንት ፎረምና ኤግዚቢሽን በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም፤ የአረንጓዴ ኢንቨስትመንት ዘርፍ የኢትዮጵያን ዘላቂ የልማት ግቦች ለማሳካትና ወደ አረንጓዴ ኢኮኖሚ የሚደረገውን ሽግግር ለማፋጠን ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ገልጸዋል። ፎረምና ኤግዚቢሽኑም ፖሊሲ አውጪዎች፣ የንግድና ዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤቶች፣ ዓለም አቀፍ የልማት አጋሮችና የአረንጓዴ ቢዝነስ ኩባንያዎችና አልሚዎች በተሳተፉበት ጳጉሜን 3 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ አስታውቀዋል። የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ በማላቅ ዘላቂ ሥነ-ምህዳራዊ ዕይታን ያማከለ የቢዝነስና የኢንቨስትመንት እንዲጎለብት ከአጋር አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም ረገድ ከጀርመን ዓለም አቀፍ የትብብር ድርጅት እና ከኔዘርላንድ የልማት ድርጅት ጋር በመተባበር የአረንጓዴ ልማትና ዘላቂነት ማዕከል ማቋቋሙን አመልክተዋል። የአረንጓዴ ኢንቨስትመንት ፎረምና ኤግዚቢሽንም ጤናማ ሥነ-ምኅዳርን የተከተለ የታዳሽ ኃይልና አረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን በማጠናከር የዘርፉ ተዋናዮች ምርትና አገልግሎታቸውን እንደሚያቀርቡ ገልጸዋል። መድረኩም በአረንጓዴ ኢንቨስትመንት ዘርፍ የተሰማሩ ባለሀብቶችን፣ የፋይናንስ ተቋማትንና ሥራ ፈጣሪዎችን በማገናኘት አዳዲስ የንግድና ኢንቨስትመንት ትስስር ዕድል እንደሚፈጥርም ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግር በማፋጠን ዘላቂ ኢንቨስትመንት ዕድሎችን ለማስፋትና የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ለማላቅም ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት አስገንዝበዋል። በኔዘርላንድ የልማት ድርጅት የሊዌይ የፕሮግራም ማኔጀር ሔለን ጌታው በበኩላቸው፤ መድረኩ ከአዲስ አበባ ንግድና የዘርፍ ማኅበራት ምክር ቤት ጋር በመተባበር የሚዘጋጅ ነው ብለዋል። ፎረሙም በአረንጓዴ ልማት ዘርፍ የተሰማሩ አልሚዎችን የፋይናንስ፣ የገበያ፣ የቴክኖሎጂና የመረጃ ተግዳሮቶች በመለየት መፍትሔ የሚመላከትበት ጠቃሚ መድረክ እንደሚሆንም ገልጸዋል። በተጨማሪም ባለድርሻ አካላትን በማገናኘት የገበያ ትስስርና የድጋፍ ዕድሎችን ለመፍጠር እንደሚያስችል አክለዋል።
የአረጓዴ ዐሻራ እና የከተሞች ልማት በአካባቢ ጥበቃና የዜጎችን ጤና በመጠበቅ ለአፍሪካውያን በአርዓያነት የሚወሰዱ ናቸው
Sep 1, 2026 147
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 26/2018 (ኢዜአ)፦የአረጓዴ ዐሻራ እና የከተሞች ልማት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋምና የዜጎችን አካላዊና አዕምሯዊ ጤና በመጠበቅ ለአፍሪካውያን በአርዓያነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን በመንግሥታቱ ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሀፊ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቡባክሪ ዲያዎ ገለጹ። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከ50 ቢሊዬን በላይ አይነተ ብዙ ችግኞችን መትከል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋምና ጤናማ ማህበረሰብ ለመገንባት ያግዛል። አዲስ አበባን ጨምሮ ከ70 በላይ በሚሆኑ ከተሞች በተዘረጋው የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻዎች ልማት ከተሞች ለነዋሪዎች ምቹ፣ ጽዱና ተስማሚ እንዲሁም ለስራ ዕድል ፈጠራ ተጨማሪ አቅም የሚፈጥሩ ሆነዋል። ኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በብዘሃ ኢኮኖሚ ዘርፍ ባከናወነቻቸው ሥራዎች ቱሪዝም ጭስ አልባው ኢንዱስትሪ ሆኖ ዕመርታ አስመዝግቧል። መከላከልና አክሞ ማዳንን መሰረት አድርጎ በተሻሻለው የጤና ፖሊሲ በመጀመሪያ ደረጃ ህክምና አገልግሎት የአፍሪካ ሞዴልነቷን በተግባር አሳይታለች። በመንግሥታቱ ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሀፊ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቡባክሪ ዲያዎ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በመጀመሪያ ደረጃ ጤና አጠባበቅ ዕምርታዊ ለውጥ አስመዝግባለች። ጤና ከማህበራዊ ወጭ ወደ ኢንቨስትመንት የሚቀየር ሀብት መሆኑን በመግለጽ፤ ዘላቂነት ያለው የጤና ሥርዓት ለመገንባት የጤና መሰረተ ልማት ግንባታን በፋይናንስ መደገፍ ይገባል ብለዋል። ጤና ለአንድ ሀገር ጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት ዕድገት የላቀ መሆኑን በማንሳት፤ ኢትዮጵያ በመጀመሪያ ደረጃ ህክምና አገልግሎት ያስመዘገበችው ስኬት ኢንቨስትመንት መሆኑ ገልጸዋል። ጤና እና የአካባቢ ጥበቃ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች መሆናቸውን የገለጹት ሃላፊው፤ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብር በቢሊዬን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል አርዓያነት ያለው ሥራ አከናውናለች ብለዋል። አዲስ አበባን ጨምሮ በተለየዩ የሀገሪቱ ከተሞች የወንዝ ዳርቻዎችን በማልማት በአካልና በአዕምሮ ጤናማ ማህበረሰብ እየገነባች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ የአረጓዴ ዐሻራ እና ከተሞች ልማት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቋቋምና ዜጎችን አካላዊና አዕምሯዊ ጤና የመጠበቅ ጥረቷን አፍሪካውያን በአርዓያነት ሊወስዱት ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራና ከተሞች ልማት ሰዎች ንጹህ አየር እየተነፈሱ የሚንሸራሸሩበትን ከተማ እየገፈጠረች መሆኑን ገልጸዋል። ይሄውም የሀገሪቱን የጤና ሥርዓት በማሻሻል የዜጎችን ጤና ከመጠበቅ ባለፈ ሳቢ የቱሪስት ማዕከል በማድረግ የኢኮኖሚ አቅሟን ያሳድጋል ብለዋል። የኢትዮጵያ ፕሮጀክቶች በእውነት ሊኮራባቸው የሚገቡ ናቸው ያሉት ሃላፊው፤ አፍሪካውያን ትምህርት በመውሰድ ከራሳቸው ነባራዊ ሁኔታ ጋር አጣጥመው መስራት እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡ አፍሪካ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተጽዕኖ ፈጣሪ ፕሮጀክቶች የሚከናወኑባት አህጉር መሆኗን ማሳየት ይገባናል ብለዋል።
የኢትዮጵያ አረንጓዴ ቃል ኪዳን
Sep 1, 2026 196
የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተጽዕኖዎች በአፍሪካ ላይ ማረፍ ከጀመሩ ሰነባብተዋል። ከተከታታይ የድርቅ ክስተቶች እስከ ከፍተኛ የጎርፍ አደጋዎች አህጉሪቷን በከፍተኛ ሁኔታ እየተፈታተኑም ይገኛሉ። ኢትዮጵያ በእነዚህና በሌሎች ፈተናዎች ውስጥ የአፍሪካ አረንጓዴ ትራንስፎርሜሽን ግንባር ቀደም ተዋናይ ሆና መጥታለች። በዚህም የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄዎችን ከወረቀት አልፎ በተግባር በመከወን ስኬታማና ተጨባጭ ስራዎችን እያከናወነች ትገኛለች። እ.አ.አ በ2011 ይፋ የሆነው የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ ከኢኮኖሚ እድገት ጎን ለጎን ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር እና ከካርቦን ነጻ የሆነ ኢኮኖሚን የመገንባት ውጥን ያለው ነው። ስትራቴጂውም አራት አንኳር ምሰሶዎች አሉት፦ የመጀመሪያው ዘላቂ ግብርና እና የቁም እንስሳት ውጤታማነትን ማሳደግ ሲሆን በዚህ ውስጥ ምርታማነትንና የአርሶ አደሮችን ገቢ መጨመር እንዲሁም የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥና ብክለትን መቀነስ ላይ ትኩረቱን አድርጓል። በደን ልማት አማካኝነት ለደኖች ጥበቃ ማድረግ፣ የደን መልሶ ልማት እና ካርቦንን አምቆ መያዝ የሚያስችሉ ግዙፍ አረንጓዴ ፕሮጀክቶችን ወደ ትግበራ ማስገባት ሁለተኛው ስትራቴጂካዊ ምሰሶ ነው። የሃይድሮ፣ የእንፋሎት፣ የንፋስ እና የፀሐይ ታዳሽ ኃይሎችን ማስፋፋት ሌላኛው የትኩረት ማዕከል መሆኑ በስትራቴጂክ ሰነዱ ላይ ሰፍሯል። በትራንስፖርት፣ በኢንዱስትሪና በመሰረተ ልማት ግንባታዎች ዘመናዊ እና ኃይል ቆጣቢ የቴክኖሎጂ አማራጮችን መጠቀም አራተኛው ጉዳይ ነው። አረንጓዴ አሻራ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ ትልቁ የተግባር ማሳያ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው አረንጓዴ አሻራ እስከ አሁን ከ54 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ተተክለዋል። የአካባቢ ጥበቃ ስራ ማህበረሰብን በግልጽ በማሳተፍ በመተግበር ላይ የሚገኝ ትልቅ ሀገራዊ ፕሮጀክት ነው። ኢትዮጵያ የኃይል ምንጭ አማራጮቿን ከታዳሽ ኃይል እያገኘች መሆኗም የስትራቴጂውን ስኬታማነት ያመላክታል። ብዝኃ የኢነርጂ አማራጮችን መጠቀም ከብክለት ነጻ የኃይል አቅርቦት እንዲገኝ እያደረገ ነው። ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ ትውልድን የሚሻገር ሁሉን አቀፍ እሳቤ ሲሆን፤ ስትራቴጂው የኢኮኖሚ እድገትን ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ያስተሳሰረና የብክለት ቅነሳን የሚያረጋግጥም ነው። በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ችግኞችን ከመትከል እስከ የታዳሽ የኃይል ምንጭን ማስፋት የኢትዮጵያ አረንጓዴ ልማት እመርታ በተግባር ገልጣ ማሳየት እያስቻላትም ይገኛል።
የሀዋሳ ከተማን ሁለንተናዊ ዕድገት የሚመጥኑ ውጤታማ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ -ከንቲባ ጥራቱ በየነ
Aug 29, 2026 215
ሀዋሳ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ የሀዋሳ ከተማን ሁለንተናዊ ዕድገት የሚመጥኑ ውጤታማ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የከተማዋ ከንቲባ ጥራቱ በየነ ገለፁ። በሀዋሳ ከተማ አስተዳደር የአካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ጽህፈት ቤት "ፅዱ ኢትዮጵያ ለትውልድ" በሚል መሪ ሀሳብ የጽዱ ኢትዮጵያ የንቅናቄ መድረክ አካሂዷል፡፡ በመድረኩ ላይ የተገኙት የአስተዳደሩ ከንቲባ ጥራቱ በየነ፤ የከተማዋን ሁለንተናዊ ዕድገት የሚመጥኑና ከተማዋን ውብ፣ ጽዱና ለኑሮ ምቹ ለማድረግ የሚያግዙ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። በከተማዋ ከኮሪደር ልማት ሥራ ጋር በተያያዘ ሰፋፊ የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች እንዲሁም በየአካባቢው የህዝብ መፀዳጃ ቤቶች መገንባታቸውንም አመልክተዋል፡፡ ሃዋሳ ውበትና ጽዳት መለያዋ መሆኑን የጠቆሙት ከንቲባ ጥራቱ፤ ከከተማዋ ዕድገትና ኢንቨስትመንት መስፋፋት ጋር ተያይዞ በቆሻሻ አወጋገድ ሥርዓት ላይ ውስንነቶች እንዳሉ ተናግረዋል። ይህንን ችግር ለመፍታት ከተማ አስተዳደሩ እየሰራ መሆኑን ገልጸው፣ በ2019 ዓ.ም የከተማዋን አድገት የሚመጥን አዲስ የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ ሥፍራ ለመገንባት ቅድመ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ከከተማዋን ሁለንተናዊ ዕድገት ጋር ተጣጥመው እየተከናወኑ ያሉ ውጤታማ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎችተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አስታውቀዋል። የሃዋሳ ከተማ የአካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዳንኤል ሹምባሻ በበኩላቸው በከተማዋ እየተከናወነ ያለው የሐይቅ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት ከአካባቢ ጥበቃ ሥራ ጋር የተሰናሰለ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በከተማዋ በየመንደሩ ቆሻሻ የሚሰበስቡና ለይተው የሚያስወግዱ ማህበራትን በማደራጀት ጽዱ አካባቢን የመፍጠር ሥራ መሰራቱን ተናግረዋል፡፡
የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከብክለት የጸዳ ከባቢና ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር አስተዋጽኦ እያደረገ ነው
Aug 28, 2026 263
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22 /2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከብክለት የጸዳ ከባቢና ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን የግሎባል ፈንድ የአፍሪካ ተወካዮች ቢሮ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዶክተር ሄንሪ ፎሙንዳም ገለጹ። በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን 76ኛው የዓለም የጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና ኮሚቴ ጉባኤ በስኬት ተጠናቋል። የአፍሪካ ሀገራት፣ ቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የጤና መሪዎች በተሳተፉበት መድረክ ላይ የኢትዮጵያ ዲጂታልና ሰው ሠራሽ አስተውሎት የታገዘ የጤና ሥርዓት ግንባታ በሽታን በመከላከልና አክሞ በማዳን አቅም ለአፍሪካውያን ምሳሌ የሚሆን ጥረት እያደረገች መሆኑ ተመላክቷል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከ50 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ለግብርና ምርታማነት፣ ለመድኃኒት ቅመማና ለአየር ንብረት ደኅንነት ውጤት እያስመዘገበች መሆኑ ተገልጿል። በመድረኩ ላይ የተገኙት ዶክተር ሄንሪ ፎሙንዳም ለኢዜአ እንዳሉት፤ በአፍሪካ ጠንካራና ዘላቂ ዋስትና ያለው የጤና ሥርዓት ለመገንባት ትብብር ወሳኝ ነው። የአፍሪካውያን ዕውቀት፣ የተፈጥሮ ጸጋና በቂ የሰው ኃይል የጤና ፋይናንስና የአስተዳደር ሥርዓቱን በማዘመን የራሳቸውን ጠንካራ የጤና ተቋማት መፍጠር እንደሚያስችላቸው ገልጸዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ የጤና እክሎችን በመቀነስ የዜጎችን በሕይወት የመኖር ምጣኔ እንደሚያሻሽል ተናግረዋል። በዚህም ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አፍሪካዊት ቀዳሚ ሀገር በመሆን ከብክለት የጸዳ ጤናማ ትውልድ ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረገች መሆኑን ተናግረዋል። አፍሪካውያን የጤና ሥርዓታቸውን በራሳቸው አቅም ለመገንባት ከአጋር አካላት ጋር የሚኖራቸው ትብብር በትይዩ እንጂ ሰጪና ተቀባይ እንዲሆን መፍቀድ እንደማይገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። የአፍሪካን የጤና ሉዓላዊነት በማረጋገጥ ከጤና የተሻገረ የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን በማሳደግ ራስን መቻል እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና በአህጉሪቷ የመድኃኒትና የሕክምና መገልገያ አምራች ኢንዱስትሪዎች መካከል ትስስር ለመፍጠር መልካም አጋጣሚ እንደሚፈጥርም አብራርተዋል።
ለትውልድ የሚተርፍ ውርስ፡የአረንጓዴ አሻራ ዘርፈ ብዙ አስተዋጽኦ
Aug 28, 2026 196
ድርቅ እና የደን መጨፍጨፍ ከኢትዮጵያ ጋር ለበርካታ ዓመታት ሲነሱ የቆዩ ጉዳዮች ናቸው። ኢትዮጵያ ይሄን ታሪኳን ለመቀየር ቆርጣ ከተነሳች ዓመታት ተቆጥረዋል።አረንጓዴ አሻራ-ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ በአካባቢ ጥበቃ እና የማይበገር የአየር ንብረት ለውጥ አቅም ግንባታ ግንባር ቀደም የሆነ የለውጥ ሞተር ሆኗል። በ2011 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ ኢኒሼቲቭ ብዝሃ ህይወትን ወደ ቀደመው ስፍራ ለመመለስ፣በረሃማነት ለመከላከል፣የደን ሽፋንን ከመጨመር አልፎ የአየር ንብረት ለውጥ የመከላከል ጥረቶች አስተዋጽኦ እስከ ማበርከት ደርሷል። የአረንጓዴ አሻራ ኢኒሼቲቭ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የዘላቂ ልማት ግቦች እና ከፓሪስ የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት ጋር በመሰናሰል ዘላቂ እና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ጠንካራ ኢኮኖሚ የመገንባት ትልም አለው። ኢኒሼቲቩ ድንበር ተሻጋሪ ተጽእኖ ያለው ነው ቢባል የተጋነነ አይሆንም።አረንጓዴ አሻራ በደን መልሶ ማልማት አማካኝነት ዛፎችን ወደ ይዞታቸው በመመለስ ወደ አየር ሊለቀቅ የሚችል በሚሊዮን ቶኖች የሚቆጠር ካርቦን ዳይ ኦክሳይድ አምቆ በመያዝ በዓለም አቀፍ ደረጃ ካርቦንዳይ ኦክሳይድን ከከባቢ አየር የማስወገድ እና የማከማቸት ጥረት ውስጥ የበኩሉን ሚና እየተጫወተ ይገኛል። የካርቦን ዳይኦክሳይድን አምቆ መያዝ እና ማከማቸት በአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስራ ውስጥ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ነው። ድንበር ተሻጋሪው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በአፍሪካ ቀንድ የመሬት መሸርሸርን ከመከላከል፣የደን ሽፋንን በመጨመር፣በረሃማነትን ከመከላከል እንዲሁም በአፈር እና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የራሱን በጎ ሚና ተጫውቷል። ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ አየር ንብረት ለውጥ ውይይቶች የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሯ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን በመቀነስ ረገድ እያበረከተ ያለው ሚና እውቅና የተሰጠው ነው። መልከ ብዙው አረንጓዴ አሻራ በአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ አዲስ አማራጭን ይዞ የመጣ እንደሆነም ይነገርለታል። ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል እና አካባቢ ጥበቃ ስራ የውጭ እርዳታ ላይ ጥገኛ ከመሆን በሀገር ውስጥ አቅም ሀብት የማሰባሰብ ሞዴል መፍጠር ችሏል። ሀገር በቀል ፋይናንስ፣የማህበረሰብ ጉልበት እና የአይነት ድጋፎች ተዳምረው በአነስተኛ በጀት ፈጠራ የታከለበት የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስራ ማከናወን እንደሚቻል አሳይቷል። ኢትዮጵያ ከአረንጓዴ አየር ንብረት ለውጥ ፈንድ (GCF)፣ የዓለም ባንክ፣የተባበሩት መንግስት የአየር ንብረት ለውጥ ፕሮግራም እና ሌሎች አጋሮች ለአካባቢ ጥበቃ ስራዎች የገንዘብ ድጋፍ እና የቴክኒክ ድጋፎችን አግኝታለች። የተገኘው ዓለም አቀፍ ድጋፍ የአካባቢ ጥበቃ ስራ በኢትዮጵያ የልማት ፖሊሲዎች የበለጠ እንዲተሳሰሩ አድርጓል። አረንጓዴ አሻራ የአየር ንብረት ለውጥ ግቦችን ከኢኮኖሚ ልማት፣ ስራ ፈጠራ፣ አረንጓዴ ቱሪዝም እና ዘላቂ ግብርና ጋር በማስተሳሰር ሁሉን አቀፍ እይታን መፍጠር ጥሏል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሀገሪቷ የደን ሽፋን መጨምርም ጉልህ ሚና ተጫውቷል። መርሃ ግብሩ ከመጀመሩ በፊት የነበረው የሀገሪቱ የደን ሽፋን 17 ነጥብ 2 በመቶ ሲሆን ባለፈው አመት በተጠናው ጥናት ሽፋኑ 23 ነጥብ 6 በመቶ መድረሱን የግብርና ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። አረንጓዴ አሻራ ከ20 ዓመት በፊት ከአራት በመቶ በታች የነበረውን የኢትዮጵያን የደን ሽፋን መልሶ እንዲያንሰራራ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። የተራቆቱ አካባቢዎችን በፍጥነት ተንከባክቦ ማዳንና ምርታማ በማድረግ፣ የተራቆተ መሬትን በእጽዋት የማልበስ ስራ ላይ ጉልህ አበርክቶ አለው። አረንጓዴ አሻራ የደን ሽፋንን ማሳደግ ብቻ ሳይሆን የደኖች ብዝሃ ህይወት ዳግም እንዲያብብና የማይበገር የአየር ንብረት ለውጥ አቅም ግንባታ ላይ የድርሻውን ተወጥቷል። በአረንጓዴ አሻራ ለደን እና ለውበት ከሚተከሉት ችግኞች ባሻገር በጥምር ደን እርሻ ለፍራፍሬ እና መኖ የሚውሉ ምግቦች በብዛት በማምረት የምግብ ዋስትና የማረጋገጥ ሂደት ውስጥ የበኩሉን ሚና እየተወጣ ይገኛል። ሲጠቃለል አረንጓዴ አሻራ ችግኝ ከመትከል ዘመቻ ያለፈ ነው።የአየር ንብረት ለውጥን የመከላከል፣ዘላቂ ልማትን የማረጋገጥ እና ዓለም አቀፍ ትብብርን የመፍጠር ትልቅ ለውጥ ያለው ኢኒሼቲቭ ነው። በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት የአየር ንብረት ግቦች እንዲሳኩ በፖለቲካ ቁርጠኝነት፣በማህበረሰብ ተሳትፎ፣ በፈጠራ መፍትሄዎች እና ሁሉን አቀፍ ተግባራት አስተዋጽኦ ማድረግ እንደሚችሉም የሚያመላክት ተምሳሌታዊ ኢኒሼቲቭ እንደሆነም ሊሰመርበት ይገባል። ዓለም በአየር ንብረት ስጋቶች ውስጥ እየኳተነች ባለችበት ወቅት የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ ልምድ የተስፋ ጮራ የሆነና አረንጓዴ ትራንስፎርሜሽን አስፈላጊ ብቻ ሳይሆን ስኬታማ ሊሆን እንደሚችል በተግባር አሳይቷል። ኢትዮጵያ ዛሬ ላይ በተፈጥሮ ላይ እየሰራች ለትውልድ መጻኢ ጊዜን እየጠበቀች ነው።ይህ ተግባር ከሀገር አልፎ ድንበርን ተሻግሯል።
የመዲናዋን የአረንጓዴ ትራንስፖርት ራዕይ እውን ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Aug 26, 2026 841
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2018 (ኢዜአ)፦የመዲናዋን የአረንጓዴ ትራንስፖርት ራዕይ እውን ለማድረግ የተከናወኑ ዘመናዊ የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶች ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገባቸውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የከተማዋን ፈጣን እድገት የሚመጥን ዘመናዊ የትራንስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታ እውን ለማድረግ በተከናወኑ የተቀናጁ ተግባራት ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውንም ጠቁመዋል። ከንቲባዋ ይህንን የተናገሩት የተገነቡ የተቀናጁ የትራንስፖርት ተርሚናሎች፣ የመኪና ማቆሚያዎችና የንግድ ማዕከላት ምረቃ መርሃ ግብር ላይ ባስተላለፉት መልዕክት ነው። ከተማ አስተዳደሩ ኅብረተሰቡ አገልግሎቶችን በፍጥነትና በጥራት የሚያገኝባቸውን በርካታ ዘመናዊ መሠረተ ልማቶች ግንባታ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት አብቅቷል ብለዋል። ዛሬው ለምረቃ የበቁት የታክሲና የአውቶቡስ አገልግሎት ትራንስፖርት የሚሰጡ መሰረተ ልማቶች ህብረተሰቡ በተረጋጋ ሁኔታ ዐረፍ ብሎ አገልግሎት እንዲያገኝ የሚያስችሉ መሆናቸውንም ገልጸዋል፡፡ ከተማዋ የጀመረችውን የአረንጓዴ ትራንስፖርት ራዕይ እውን ለማድረግ በትራንስፖርት መሰረተ ልማት ግንባታዎቹ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ሀይል መሙያዎች መካተታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የከተማዋን የትራፊክ ፍሰት ማቃለል የሚያስችሉ ሰፋፊ የመኪና ማቆሚያዎች ከነሙሉ አገልግሎታቸው ተዘጋጅተው ለሕዝብ ጥቅም ክፍት ተደርገዋል ነው ያሉት፡፡ ከተማ አስተዳደሩ የህብረተሰቡን የትራንስፖርት አገልግሎት ፍላጎት ከመመለስ ባሻገር የአካባቢ ጥበቃን ያማከሉ አረንጓዴ የትራንስፖርት አማራጮችን እያሰፋ እንደሚገኝም ከንቲባ አዳነች ገልጸዋል፡፡ በዚህም በመዲናዋ አረንጓዴ ትራንስፖርትን ለመገንባት በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል ሲሉም ተናግረዋል፡፡ እነዚህ የትራንስፖርት አገልግሎት መስጫ መሰረተ ልማቶች ከተማዋ ወደ አረንጓዴ ትራንስፖርት የምታደርገውን ሽግግር ያፋጥናሉ ብለዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የህዝብ ትራንስፖርትንና የግል ተሽከርካሪዎችን ጨምሮ የመኪና ማቆሚያ አቅም ከ180 ሺህ በላይ መድረሱን ከንቲባዋ ጨምረው አስታውቀዋል፡፡ በእነዚህ የትራንስፖርትና የመኪና ማቆሚያ መሰረተ ልማቶች ግንባታና አገልግሎት አሰጣጥ ብቻ እስከ አሁን ከ20 ሺህ በላይ ለሆኑ ወጣቶች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዲዛይንና ግንባታ ሥራዎች ቢሮ ኃላፊ ኢንጂነር አያልነሽ ሐብተማሪያም በበኩላቸው፤ ቢሮው ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ፍጥነትና ጥራት ተጠናቅቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ ብርቱ ክትትል ሲያደርግ መቆየቱን ጠቅሰዋል፡፡ መሰረተ ልማቶቹ የትራፊክ ፍሰቱን የሚያቀላጥፉና የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ሀይል መሙያዎችን ያካተተ መሆኑን ጠቅሰዋል። በውስጣቸው የንግድ ሱቆች፣ ካፌና ሬስቶራንቶች፣ አሳንሰሮችና የቲኬት መቆረጫ ቢሮዎች እንደተገነባላቸውም ገልጸዋል።
በኦሮሚያ ክልል የተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራና የተፈጥሮ ጥበቃ ስራዎች የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የሚደረገውን እንቅስቃሴ እያገዙ ነው
Aug 24, 2026 391
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 18/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል የተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራና የተፈጥሮ ጥበቃ ስራዎች የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የሚደረገውን እንቅስቃሴ እያገዙ እንደሚገኙ የክልሉ ደን እና ዱር እንስሳት ድርጅት አስታወቀ። በክልሉ ደረጃ እየተካሄደ ያለው የካርበን ሽያጭ በአለም አቀፍ ደረጃ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ለሚደረገው ጥረት የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝም ተገልጿል። የኦሮሚያ ክልል ደን እና ዱር እንስሳት ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ አራርሳ ረጋሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ክልሉ ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በሚደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። በተለይም የካርቦን ዳይኦክሳይድ ልቀትን በመቀነስ የምድር ሙቀትን ለመግታትና የደን ሽፋን ለማሳደግ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙ አመላክተዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተተከሉት ችግኞች መካከል አብዛኞቹ ጸድቀው ወደ ደንነት በመሸጋገራቸው የአካባቢውን አየር ንብረት በመጠበቅና የካርቦን ልቀትን በመቀነስ በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ እያበሩከቱ ይገኛሉ ብለዋል። ህብረተሰቡም ከተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ዘላቂ ተጠቃሚ የሚሆንበት አሰራር ተዘርግቶ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን የመቋቋም አቅምን የማጠናከሩ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት። አቶ አራርሳ ጨምረው እንደገለጹት፤ ክልሉ የደን ካርበን ንግድን በማስፋፋት በአለም አቀፍ ደረጃ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ለሚደረገው ጥረት የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። በተደረገው ሳይንሳዊ ጥናት መሠረት አንድ ሄክታር የደን መሬት ከ10 እስከ 20 ቶን የሚደርስ ካርቦን ዳይኦክሳይድ በውስጡ የመያዝ እና የማመቅ ከፍተኛ አቅም እንዳለው አብራርተዋል። ይህም ክልሉ የሚያካሂደው የደን ልማት ለአለም አቀፉ የካርቦን ልቀት ቅነሳ ጥረት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ማረጋገጫ እንደሆነ አብራርተዋል። አቶ አራርሳ ኢትዮጵያ ከካርቦን ገበያ ገቢ ማግኘት የጀመረችበትን ታሪካዊ ሂደት ሲያብራሩ፤ የመጀመሪያው የደን ካርበን ሽያጭ እ.ኤ.አ በ2012 በባሌ ደን መጀመሩን አውስተዋል። እ.ኤ.አ ከ2012 እስከ 2019 ባለው ጊዜ ውስጥም 9 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ካርቦን ለገበያ በማቅረብ ወደ ግማሽ ቢሊዮን ብር የሚጠጋ ገቢ ተገኝቷል። ከሽያጩ የተገኘው ገቢም ደኑን ለጠበቁ የአካባቢው ነዋሪዎች እና ለቀጣይ የደን ልማት ስራዎች በመዋሉ የማህበረሰቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል። ድርጅቱም ከአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ አጋሮች ጋር በመቀናጀት እ.ኤ.አ ከ2022 እስከ 2024 ባሉት ዓመታት የተመዘገበውን 13 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን የካርቦን መጠን ለገበያ ለማቅረብ ዝግጁ ሆኗል። በቀጣይም የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ደኖችን በሳይንሳዊ መንገድ በመንከባከብና የካርቦን ንግድን በመተግበር የአካባቢ ጥበቃውን እንዲሁም ሀገራዊ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን የማሳደግ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ውበትን ከስልጣኔ ጋር ያቆራኙ የኮሪደርና የወንዝ ዳር ልማቶች
Aug 23, 2026 342
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 17/2018 (ኢዜአ)፦ በመዲናዋ በኮሪደር እና በወንዝ ዳር ልማቶች የተገነቡት ቤተ መጽሐፍት እና የተለያዩ የመዝናኛ ስፈራዎች ለመጪው ትውልድ ብሩህ ተስፋን የሰነቁ የስልጣኔ ማሳያዎች መሆናቸውን ኢዜአ ያነጋገራቸው የማህበረሰብ ክፍሎች ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር መዲናዋን ዓለም አቀፍ ደረጃዋን የጠበቀች፣ ለነዋሪዎቿ ምቹና ዘመናዊ ለማድረግ እያከናወነ የሚገኘው ግዙፍ የኮሪደር ልማት ስራ የከተማዋን ገጽታ ከመቀየር ባለፈ በማህበረሰቡ የዕለት ተዕለት የኑሮ ዘይቤ ላይ አዎንታዊ ለውጥ እያመጣ ይገኛል። ይህ በዋና ዋና አደባባዮች፣ መናፈሻዎች፣ መንገዶችና የወንዝ ዳርቻዎች ላይ ያተኮረው የመሠረተ ልማት ዝርጋታ፤ ውበትን ከጥቅም ጋር አዋህዶ የያዘ በመሆኑ ከፍተኛ ለውጦችን እያመጣ ነው። ኢዜአ ያነጋገራቸው የህብረተሰብ ክፍሎች እንደሚሉት፤ የተገነቡት የመጫወቻና የማንበቢያ ስፍራዎች የከተሜነት ምህዳሩን ከማሻሻላቸው ባሻገር ለወጣቶች የማሰላሰያና አዳዲስ ሐሳቦችን ማፍለቂያ ማዕከላት እየሆኑ ነው። ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል ወይዘሮ ጺዮን ጌታቸው፤ በቅርብ ዓመታት የተከናወኑት የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማቶች አዲስ አበባን ለኑሮ ተስማሚ ከማድረጋቸው ባሻገር፣ ነዋሪው አእምሮውን እያዝናና እውቀት እንዲገበይበት መንገድ መክፈታቸውን ገልጸዋል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ግርማ አለሙ በበኩላቸው፤ ፕሮጀክቶቹ መጪውን ትውልድ ታሳቢ ያደረጉና ለአዲሱ ትውልድ ጠንካራ መሰረት የሚጥሉ መሆናቸውን ጠቁመው፣ በተለይም የተዘጋጁት የንባብ ማዕከላት ለተለያዩ ጥናትና ምርምሮች ከፍተኛ ፋይዳ እንዳላቸው ተናግረዋል። የመዲናዋ ነዋሪ ወጣት ፍራኦል ናትናኤል በበኩሉ የኮሪደር ልማቱ የሀገሪቱን መልካም ገጽታ በመገንባት በኩል የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ ነው ብሏል። ይህም ለአገር ውስጥና ለውጭ ኢንቨስትመንት መሳብ ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥር ገልጿል። አቶ እንዲሪስ ተሾመ እና አቶ ግርማ ንጉሴ የተባሉ ነዋሪዎች በሰጡት አስተያየት፤ በአሁኑ ወቅት በመዲናዋ ደረጃቸውን የጠበቁ በርካታ የመዝናኛ ስፍራዎች ተገንብተዋል ብለዋል። አሁን ላይ ከቤተሰቦቻቸው ጋር የእረፍት ጊዜ ለማሳለፍ እነዚህን አካባቢዎች ምርጫቸው ማድረጋቸውን ተናግረዋል። የወንዝ ዳርቻ ልማቶቹ፣ የሕዝብ ቤተ-መጻሕፍትና የመዝናኛ ስፍራዎቹ የከተማዋን ውበትና የህዝቡን የማህበራዊ ህይወት ደረጃ ያሳደጉ መሆናቸውን ገልጸዋል።
አካባቢን ከብክለት በመጠበቅ ጤናማና አምራች ዜጋን የማፍራቱ ተግባር ይጠናከራል
Aug 21, 2026 417
ገንዳውሃ፤ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ)፡- ህብረተሰቡ አካባቢውን ከብክለት በመጠበቅና በማፅዳት ጤናማና አምራች ዜጋን የማፍራት ተግባርን አጠናክሮ እንዲቀጥል የምዕራብ ጎንደር ዞን አካባቢና ደን ጥበቃ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር "ፅዱ ኢትዮጵያ ለትውልድ" በሚል መሪ ሐሳብ የተዘጋጀ የሀገራዊ እንቅስቃሴ አካል የሆነ የፅዳት ዘመቻ ዛሬ ተካሄዷል። የምዕራብ ጎንደር ዞን አካባቢና ደን ጥበቃ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሮ መልካም ዋሲሁን በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፣ ፅዱና ውብ አካባቢን መፍጠር ለጤናማ ማኅበረሰብ ግንባታ መሠረት ነው። አካባቢን ከፕላስቲክና ከሌሎች ደረቅ እንዲሁም ፈሳሽ ቆሻሻዎች ነፃ በማድረግ ፅዱ አካባቢን መፍጠር አምራች፣ ጤናማና ውጤታማ ትውልድ ለማፍራት ወሳኝ ድርሻ እንዳለው ተናግረዋል። ለዚህም ማኅበረሰቡ የአካባቢ ፅዳት ሥራን የአንድ ወቅት ዘመቻ ሳያደርግ የዘወትር ተግባርና የኑሮ ባህሉ በማድረግ ኃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባም አሳስበዋል። የዞኑ ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ ዮሴፍ ጉርባ በበኩላቸው፣ ከአካባቢ ንፅህና ጉድለት ጋር ተያይዘው የሚመጡ ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል ሕብረተሰቡ የግልና የአካባቢውን ንፅህና ዘወትር ሊጠብቅ ይገባል ብለዋል። አካባቢው ሞቃታማ በመሆኑ እንደ ወባ፣ ኮሌራና መሰል ተላላፊ በሽታዎች በወረርሽኝ መልክ እንዳይከሰቱ የግልና የአካባቢን ንፅህና መጠበቅ ባህል ሊደረግ ይገባል ነው ያሉት። የገንዳውኃ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ተወካይ አቶ አዳነ ሀሰን እንዳሉት፣ ከተማዋን ለነዋሪዎቿ ምቹና ለባለሀብቶች ሳቢ ለማድረግ በአካባቢ ንፅህና አጠባበቅ ላይ በትኩረት እንደሚሠራ ገልጸዋል። የከተማዋ ነዋሪዎች፣ የንግዱ ማኅበረሰብና የወጣት አደረጃጀቶች አካባቢያቸውን ሰላም ከመጠበቅ ጎን ለጎን ፅዱና ለኑሮ ተስማሚ ለማድረግ የጀመሩትን ተሳትፎ አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጥሪ አቅርበዋል። "ለነገው ሀገር ተረካቢ ሕፃናት ፅዱ ከተማን ማስረከብ የእኛ የወጣቶች ኃላፊነት ነው" ያለው ደግሞ በፅዳት ዘመቻው የተሳተፈው ወጣት ሃብታሙ አክሊሉ ነው። ከተማዋን ከፕላስቲክና ከሌሎች መርዛማ ኬሚካሎች በማፅዳት ማራኪና ለነዋሪዎቿ የምትመች ተመራጭ ከተማ ለመፍጠር በሚደረገው ሂደት በቀጣይም የድርሻውን እንደሚወጣ አረጋግጧል። በፅዳት ዘመቻው የከተማዋ የመንገድ ዳርቻዎች፣ የገበያ ስፍራዎችና የሕዝብ መዝናኛ አካባቢዎችን ከቆሻሻ ፅዱ የማድረግ ሥራ የተከናወነ ሲሆን፣ በየሳምንቱም የፅዳት ዘመቻው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ከወጣው መርሃ ግብር ለመረዳት ተችሏል። በተካሄደው የፅዳት ዘመቻም የዞኑና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ የመንግሥት ሰራተኞች፣ የአካባቢው ነዋሪዎችና የተለያዩ አደረጃጀቶች ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያ በሰው እና በአካባቢ ላይ ጉዳት የሚያስከትሉ የማይመክኑ ኦርጋኒክ በካዮችን ለመቆጣጠርና ለማስወገድ በትኩረት እየሰራች ነው
Aug 21, 2026 393
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15 /2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በሰው እና በአካባቢ ላይ ጉዳት የሚያስከትሉ የማይመክኑ ኦርጋኒክ በካዮችን (POPs) ለመቆጣጠርና ለማስወገድ በትኩረት እየሰራች መሆኑን የኢፌዴሪ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። ባለስልጣኑ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር የተሻሻለ የብሔራዊ የትግበራ እቅድ ሰነድ ግምገማ እና ማጽደቂያ መድረክ አካሂዷል። የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ በዚሁ ወቅት፤ የማይመክኑ ኦርጋኒክ በካዮች በባህሪያቸው ቶሎ የማይበሰብሱ፣ በሰው እና በአካባቢ ላይ ጉዳት የሚያስከትሉ ቁሶች ናቸው ብለዋል። ከእነዚህ ውስጥም ዲዲቲ (DDT)፣ ፒፎስ (PFOS) እና ፒኤፍኤችኤክስኤስ (PFHxS) የተሰኙትን ለአብነት አንስተዋል። የማይመክኑ ኦርጋኒክ በካዮች (POPs) የሚያስከትሉትን ጉዳት ለመከላከልና ለማስወገድ ጥቅም ላይ እንዳይውሉ ወይም እንዳይመረቱ የሚያደርግ እኤአ በ2001 የስቶክሆልም ስምምነት መደረጉን አውስተዋል። ኢትዮጵያ ስምምነቱን መሰረት በማድረግ በሰው እና በአካባቢ ላይ ጉዳት የሚያመጡ የማይመክኑ ኦርጋኒክ በካዮችን (POPs) ለመቆጣጠርና ለማስወገድ ዘርፈ-ብዙ ተግባራትን እንዳከናወነች ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደም ለተለያዩ አላማዎች በሚል ይመረቱ የነበሩ እንደ ዲዲቲ (DDT) ያሉ የማይመክኑ በካዮች እንዳይመረቱ እንዲሁም ሀገር ውስጥ ማምከኛ የሌላቸው የተለያዩ ኬሚካሎችን ወደ ውጭ በመላክ እንዲመክኑ መደረጉን አስታውቀዋል። ዛሬ ለምክክር የቀረበው ሰነድ በሀገር ደረጃ የማይመክኑ ኦርጋኒክ በካዮች አያያዝ፣ ቁጥጥር እና አስተዳደርን የሚያጠናክር ተግባራዊ የስራ መመሪያ መሆኑን ገልጸዋል። መድረኩ አሁን በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተካሄደ ካለው ሶስተኛ ዙር "ጽዱ ኢትዮጵያ ለትውልድ" ስራ ጋር ተያያዥነት ያለው እንደሆነም አመላክተዋል። ለብሔራዊ ትግበራ መርሃ ግብሩ ስኬት የፌደራልና የክልል ተቋማት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ የግሉ ዘርፍ፣ የሲቪል ማህበራት እና የልማት አጋሮች ቅንጅት ወሳኝ መሆኑንም ምክትል ዋና ዳይሬክተሯ ጨምረው ተናግረዋል። አዳዲስ በካይ ኬሚካሎችን መለየት፣ የላቦራቶሪ ቁጥጥር አቅምን ማሳደግ፣ ማምከኛ መሳሪያዎችን መታጠቅ፣ የመረጃ ስብሰባን ማጠናከርና የቴክኒክ እንዲሁም የፋይናንስ አቅምን ማጎልበት የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ናቸው ብለዋል። ከመድረኩ የተገኙት ግብዓቶችን በማካተት ሰነዱን የበለጠ ለማጠናከርና ውጤት ተኮር ለማድረግ እንደሚሰራም አረጋግጠዋል።
በኦሮሚያ ክልል ተመናምኖ የነበረው የደን ሽፋን በአረንጓዴ አሻራ አማካኝነት በፍጥነት እያደገ ነው
Aug 21, 2026 325
አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 15/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተከናወኑ ተግባራት አማካኝነት ተመናምኖ የነበረው የደን ሽፋን መልሶ እድገት እያሳየ መሆኑን የክልሉ ደን እና ዱር እንስሳት ድርጅት አስታወቀ። የኦሮሚያ ክልል ሰፊ የተፈጥሮ ሀብትና ብዝሃ-ሕይወት ባለቤት ቢሆንም፣ ባለፉት አሥርተ ዓመታት በሕገ-ወጥ የደን ምንጣሮ፣ ለእንጨትና ከሰል ምርት በሚደረግ ጭፍጨፋ እና ለእርሻ መሬት ማስፋፊያ ምክንያት የደን ሽፋኑ በከፍተኛ ደረጃ ተመናምኖ ቆይቷል። ይህ የደን ውድመት አካባቢውን ለአፈር መሸርሸር፣ ለወንዞችና ሐይቆች መድረቅ እንዲሁም ለምርታማነት መቀነስ ዳርጎት የነበረ ሲሆን፣ በተለይም እንደ ሐረማያ ባሉ አካባቢዎች የነበሩ የውሃ አካላት ሙሉ በሙሉ እስከመድ ረቅ ደርሰው የነበረው አካባቢያዊ ሥነ-ምህዳሩ ለከፍተኛ አደጋ ተጋልጦ ስለነበር ነው። ይህንን ሥነ-ምህዳራዊና ምጣኔ-ሀብታዊ አደጋ ለመቀልበስ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢኒሼቲቭ በሀገር ደረጃ እየተካሄደ ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በክልሉም በየዓመቱ እንደ ዋነኛ መፍትሔ ተወስዶ ሰፊ የተቀናጀ ንቅናቄ በማካሄድ በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ውጤት እየመጣ ነው። የኦሮሚያ ክልል ደን እና ዱር እንስሳት ድርጅት ሥራ አስኪያጅ አቶ አራርሳ ረጋሳ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ በክልሉ ባለፉት ዓመታት የደን ሽፋኑን ለማሳደግ የተለያዩ ተግባራት ተከናውነዋል። በክልሉ የደን ሽፋኑን ለማሳደግ ከተከናወኑት ተግባራት መካከል፣ በተለይም በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተራቁተው በነበሩ ቦታዎች ላይ ሳይንሳዊ መንገድን በተከተለ መልኩ የተለያዩ ችግኞች መተከላቸውን ተናግረዋል። ከዚህ ጎን ለጎን አካባቢዎችን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ነፃ በማድረግ እንዲሁም ሕገ-ወጥ የእርሻ መሬት ማስፋፋትን ለመግታት በተሠራው ሥራ ከፍተኛ ውጤት መመዝገቡን ተናግረዋል። በተለይም ችግኞችን በመትከል ላይ ብቻ ሳይወሰን ለእንክብካቤያቸው ከፍተኛ ትኩረት በመሰጠቱ ለውጤቱ ዋነኛ ምክንያት መሆኑን አብራርተዋል። በዚህም በክልሉ ከዚህ በፊት ተመናምኖ የነበረው የደን ሽፋን ወደ 27 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ስራ አስኪያጁ ተናግረዋል። ይህ የተቀናጀ ጥረት የአፈር መንሸራሸርን መከላከል፣ የአፈር ለምነትን መመለስ እንዲሁም የደረቁ ምንጮች፣ ሀይቆችና ወንዞች እንደገና እንዲጎለብቱ ያደረገ ሲሆን፣ በዚህም በምስራቅ ሀረርጌ ዞን ደርቆ የነበረው የሐረማያ ሀይቅ ሙሉ በሙሉ ማገገሙን ለአብነት አንስተዋል። በአጠቃላይ የመርሃ ግብሩ ስኬት በሁሉም ወቅቶች መሬትን በማልማት፣ የአካባቢ ጥበቃን ከግብርና ስራዎች ጋር በማጣመር የምርትና ምርታማነት እድገትን ከማሳደግ አንጻር ከፍተኛ ድርሻ እያበረከተ እንደሚገኝ ተናግረዋል። አቶ አራርሳ እንደገለጹት፣ በአሁኑ ወቅት በክልሉ በአጠቃላይ 4 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በደን መልማቱን ገልጸዋል። ከአጠቃላይ መሬቱ ውስጥ 1 ሚሊዮን ሄክታር ያህሉ ለዱር እንስሳት እንክብካቤና ጥበቃ፣ ለፓርኮች፣ ለስፖርት ስፍራዎች ሲሆኑ፣ 700 ሺህ ሄክታር መሬት ደግሞ ለችግኝ ተከላ እና ለሰው ሰራሽ ደን ልማት የተመደበ ስፍራ ነው። ከአጠቃላይ መሬቱ 2 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ደግሞ ሙሉ በሙሉ በተፈጥሮ ደን የተሸፈነ መሆኑን አስታውቀዋል።