አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በዞኑ ከ6 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት መልሶ እንዲያገግም የማድረግ ተግባር እየተከናወነ ነው
Mar 19, 2024 28
ሽሬ እንዳስላሴ ፤ መጋቢት 10/2016(ኢዜአ)፦ በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች የተመናመኑ ከ6 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት መልሶ እንዲያገግም ለማድረግ እየተከናወነ መሆኑን በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን የተፈጥሮ ሀብት ፅህፈት ቤት አስታወቀ። አስተባባሪው አቶ ሃብተስላሴ አሰፋ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በዞኑ በሚገኙ አራት ወረዳዎች የሚገኝ ከ6 ሺህ ሄክታር በላይ ደን መልሶ እንዲያገግም ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ በመከለል ጥበቃና እንክብካቤ እየተደረገለት ነው። በአካባቢው ነዋሪዎች ተሳትፎ ተከልሎ እንዲጠበቅና እንክብካቤ እየተደረገለት ያለው ደን በአብዛኛው ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ባለው የእጣን ዛፍ የተሸፈነ እንደሆነ አስተባባሪው ገልፀዋል። ጉዳት የደረሰበት ይኸው የተፈጥሮ ደን መልሶ እንዲያገግም በህዝብ ነፃ ተሳትፎ የተለያዩ ጎርፍ አልባ እርከኖች እየተገነቡለት መሆኑን አስረድተዋል። እንዲሁም ጉዳት የደረሰበትን የደን ክፍል መልሶ ለማልማት የተለያዩ አገር በቀል ችግኞችን ለመትከል የችግኝ ማፍላት ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። ደኑ ሙሉ በሙሉ ካገገመ በኋላ በማህበር የተደራጁ ወጣቶች ንብ በማነብና እጣን በማምረት ተጠቃሚ እንዲሆኑ እድል እንደሚፈጠርላቸውም አስተባባሪው ተናግረዋል። በዞኑ አስገደ ወረዳ ፀሊሞይ በተባለ የገጠር ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ገብረመድህን በላይ በሰጡት አሰተያየት በተከለለው ደን ውስጥ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራ በማከናወን ደኑ መልሶ እንዲለማና ወደ ቀድሞ ይዞታው እንዲመለስ ጥረት እያደረጉ እንደሆነ ገልፀዋል። ሌላው የዚሁ ገጠር ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር አስገደ ግርማይ በበኩላቸው ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ነፃ ሆኖ እንዲከለል የተደረገው ደን ሙሉ በሙሉ አስኪያገግም ከመጠበቅና ከመንከባከብ ወደ ኋላ እንደማይሉ ቃል ገብተዋል። በዞኑ በደን የተሸፈነው 52 ሺህ ሄክታር መሬት በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች የተጎዳ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን በክልሉ በሰፈነው ሰላምም በየዓመቱ ቢያንስ ከአምስት ሺህ በላይ ሄክታር ደን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ነጻ በማድረግ መልሶ እንዲያገግም እየተሰራ መሆኑን ከዞኑ የተገኘው መረጃ ያሳያል።
የለሙ ተፋሰሶች የገቢ ምንጭ ሆኖናል- በማዕከላዊ ጎንደር አርሶ አደሮች
Mar 19, 2024 58
ጎንደር፣መጋቢት 10 / 2016(ኢዜአ)፡-በአካባቢያቸው ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ሥራዎች የለሙ ተፋሰሶችን ለገቢ ማስገኛ በማዋል ተጠቃሚ መሆናቸውን በማዕከላዊ ጎንደር ዞን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ በዞኑ አርሶ አደሮች ከሰብል ማምረት ባሻገር የለሙ 144 ተፋሰሶችን ተጠቅመው በንብ ማነብ፣ በእንስሳት ማድለብና በፍራፍሬ ልማት ላይ መሰማራታቸውን የዞኑ ግብርና መምሪያ አመልክቷል፡፡ አርሶ አደር መንበሩ ቻላቸው በላይ አርማጭሆ ወረዳ የግንድ መጣያ ቀበሌ ነዋሪ ሲሆኑ፤ ባለፉት ዓመታት በአካባቢያቸው የተከናወነው ተፋሰስ ልማት ለእንስሳት መኖ አቅርቦት ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ለኢዜአ ተናግረዋል። በዚህም ሁለት በሬዎችን አድልበው ሸጠው ካገኙት 120 ሺህ ብር ገቢ ሁለት የወተት ላሞችን ባለፈው ክረምት መግዛታቸውን ገልጸዋል። በላሞቹ በቀን 15 ሊትር ወተት በማለብና ለጎንደር ከተማ ገበያ በማቅረብ ገቢ እያገኙ መሆኑን አመልከተዋል፡፡ የምዕራብ ደንቢያ ወረዳ አርሶ አደር ሙላት በየነ በበኩላቸው፤ ተፋሰስን መሰረት በማድረግ ስድስት ዘመናዊ የንብ ቀፎዎችን በመጠቀም የማነብ ስራውን አጠናክረው መቀጠላቸውን ተናግረዋል። ባለፈው መኸርም ከስድስቱ ቀፎዎች 180 ኪሎ ግራም ማር በመቁረጥ ለገበያ አቅርበው በመሸጥ 63ሺህ ብር ገቢ ማግኘታቸውን አስረድተዋል፡፡ በአካባቢያቸው በሚገኝ ተፋሰስ ያለሙት የአቦካዶ ፍራፍሬ አሁን ላይ ምርት መስጠት መጀመሩን የገለጹት ደግሞ በጎንደር ዙሪያ ወረዳ የምጥርሃ ቀበሌ አርሶ አደር ሞላ ግስሜ ናቸው። ባለፉት ዓመታት በተከታታይ የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ በማከናወን የመሬታቸው የአፈር ለምነት መጨመሩን አመልክተው፤ ምርታማነቱ ከፍ እያለ ተጠቃሚነታቸውም እያደገ መሆኑን አብራርተዋል። የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በዞኑ በለሙ 144 ተፋሰሶች ከአራት ሺህ በላይ አርሶ አደሮች ከሰብል ማምረት ባሻገር ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ሆኗቸዋል። አርሶ አደሮቹ ተፋሰሶች ውስጥ በንብ ማነብ፣ በእንስሳት ማድለብና በፍራፍሬ ልማት ዘርፍ የተሰማሩ የዞኑ አርሶ አደሮች በግማሽ የበጀት ዓመቱ ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ በማግኘት ተጠቃሚ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ በተጨማሪም በተፋሰሶቹ በንብ ማነብ ስራ የተሰማሩ አርሶ አደሮች ከ20ሺህ ኪሎ ግራም በላይ ማርና 10ሺ የደለቡ የእርድ እንስሳት ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚነታቸውን ማሳደግ መቻላቸውን ጠቁመዋል፡፡ በማዕከላዊ ጎንደር ዞን ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት ስራዎች ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ የተከለሉ አንድ ሺህ 236 ተፋሰሶች እንደሚገኙ ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያሳያል፡፡
በአገሪቱ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖዎች ለመቋቋም በገጠር ቀበሌዎች በመተግበር ላይ የሚገኙ ፕሮጀክቶች ውጤቶች እያስገኙ ነው
Mar 18, 2024 99
ድሬዳዋ ፤ መጋቢት 9/2016 (ኢዜአ)፡- በአገሪቱ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖዎች ለመቋቋም በገጠር ቀበሌዎች በመተግበር ላይ የሚገኙ የልማት ፕሮጀክቶች ውጤቶች እያስገኙ መሆናቸው ተመለከተ። በገንዘብ ሚኒስቴር አስተባባሪነት በመንግስትና በ'ግሪን ክላይሜት ፈንድ' በድሬዳዋ ገጠር ቀበሌዎች በተሰሩ ልማቶች ላይ ውይይትና የልምድ ልውውጥ እየተካሄደ ነው። ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት እየተገበረ ያለው ስትራቴጂ ዕውን እንዲሆን እየደገፉ ከሚገኙ መካከል አንዱ በመንግስትና በ'ግሪን ክላይሜት ፈንድ' የሚተገበሩ ፕሮጀክቶች ተጠቃሽ ናቸው። በ50 ሚሊዮን ዶላር ለድርቅ ተጋላጭ በሆኑ 66 የአገሪቷ ቀበሌዎች በመተግበር ላይ የሚገኘው ይህ ፕሮጀክት በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ ለድርቅ ተጋላጭ የሆኑ 330 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎችን በቀጥታና 930 ሺህ የሚሆኑትን ደግሞ በተዘዋዋሪ በዘላቂነት ለመቋቋም እንዲችሉ ማገዝ እንደሆነ ተገልጿል። በገንዘብ ሚኒስቴር የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ምስጋናው እያሱ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ባለፉት አራት ዓመታት በ66 የአገሪቷ ገጠር ቀበሌዎች በፕሮጀክቱ የተከናወኑ ስራዎች አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመፍጠር የሚሰሩ ስራዎችን በማገዝ ረገድ አበርክቶው የጎላ ነው። በድሬዳዋ ዛሬ የተጀመረው አገር አቀፍ የልምድ ልውውጡ በድሬዳዋ አምስት ገጠር ቀበሌዎች የተከናወኑት የተፈጥሮ ሃብትና የውሃ ጥበቃ እንዲሁም የደን ልማት ስራዎችን በመገምገም የተሻለ ተሞክሮ ለመቀመር ያስችላል ብለዋል። የተከናወኑት የንጹህ መጠጥና የአነሰተኛ መስኖ የውሃ ፕሮጀክቶች፣ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና የደን ልማት ፕሮጀክቶች ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚን ለመፍጠር የተጀመረው የተቀናጀ ጥረት እንዲጠናከር የሚያግዙ መሆናቸውን ገልፀዋል። በድሬዳዋ የተጀመረው በሐረሪ ክልልም ቀጥሎ የሚካሄደው የተሞክሮ ልውውጥን በመቀመር በቀጣይ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ይሰራል ብለዋል። የድሬዳዋ ፕሮጀክቶችን የሚያስተባብረው የአስተዳደሩ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሙሉካ መሐመድ በበኩላቸው፤ በመንግስትና በ"ግሪን ክላይሜት ፈንድ" የተተገበሩ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና የውሃ ሃብት የማልማት ስራዎች በቤተሰብ ደረጃም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎችን እያገዙ ናቸው ብለዋል። የተጠናቀቁት የንጹህ መጠጥ ውሃና የአነስተኛ መስኖ ስራዎች የገጠሩን ህብረተሰብ ማህበራዊ ችግሮች እያቃለሉና የገቢ ምንጭን እያሳደጉ መሆናቸውን ለአብነት በማንሳት። እነዚህ ጅምር ውጤታማ ተግባራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባት እየተሰራ ያለውን ስትራቴጂ ስኬታማ እንዲሆን እያገዙ መሆናቸውን ነው የገለፁት። ከገንዘብ ሚኒስቴር እና ሌሎች አጋር ተቋማት የተውጣጡ የአመራር አባላት በድሬዳዋ ገጠር ቀበሌዎች የተከናወኑ ፕሮጀክቶችን ከነገ ጀምሮ እስከ ሚቀጥለው ሐሙስ እንደሚመለከቱም ከወጣው መርሃ ግብር ለማወቅ ተችሏል።
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ስራ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች እየተገኙ መሆኑ ተገለጸ
Mar 17, 2024 138
አሶሳ፤ መጋቢት 8/2016(ኢዜአ)፦ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ስራዎች ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች እየተገኙ መሆኑ ተገለጸ። በክልሉ ግብርና ቢሮ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ ፍቃዱ ደሳለኝ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ ካለፈው የካቲት ወር አጋማሽ የተጀመረው የዘንድሮ የበጋ ተፋሰስ ልማት ዘመቻ ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ ለሁለት ወራት በሚካሄደው በዚሁ ዘመቻ ባለፉት ሁለት ሳምንታት ውስጥ 15 ሺህ 500 የሚጠጋ ሄክታር መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ስራ ተከናውነዋል ብለዋል፡፡ በተፋሰስ ልማቱ ከሁለት ሚሊዮን በላይ የክልሉ ነዋሪዎች መሳተፋቸውን ዳይሬክተሩ አስረድተዋል፡፡ የበጋ ተፋሰስ ልማት ዘመቻው በእስካሁን ስራ የተሳተፉ ሰዎች በጉልበት ሲለካም ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ እንደሆነ አቶ ፍቃዱ አመልክተዋል፡፡ ስራው እስከ መጋቢት ወር መጨረሻ እንደሚቀጥል ጠቁመው፤ እቅዱን ለማሳካት ስልጠናን ጨምሮ የተፈጥሮ ሃብት ባለሙያዎች ተከታታይ ክትትልና ድጋፍ እያካሄዱ መሆኑን ነው የገለጹት፡፡ በተፋሰስ ልማት እየተሳተፉ ከሚገኙ የክልሉ አርሶ አደሮች መካከል በአሶሳ ዞን የብራሞ ወረዳ ነዋሪ አቶ አደም ይመር እንዳሉት ባለፉት 10 ዓመታት በዘመቻ በተከናወኑ የበጋ ተፋሰስ ስራ የተራቆቱ አካባቢዎች መልሰው አገግመዋል፡፡ በዚህ ዓመት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራውን ያከናወኑባቸው ቦታዎች ከእንስሳት እና ሌሎችም ንክኪዎች በመጠበቅ በመጪው ክረምት ችግኝ ተከላ ለማስቀጠል መዘጋጀታቸውን አስረድተዋል፡፡ የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ተበጀ ጌታሁን በበኩላቸው በተፋሰስ ልማት ስራው ከጥቅም ውጪ የሆነ መሬት እንዲያገግም ማስቻሉ ተናግረዋል ፡፡ የተፋሰስ ልማት በተከናወነባቸው ስፍራዎች የተተከሉ ማንጎ፣ አቮካዶ፣ ፓፓዬ እና ሌሎችም ተክሎች ለምግብነት እየተጠቀሙ መሆኑን አመልክተዋው የቤት እንስሳትም በቂ መኖ እንዲያገኙ ማስቻሉንም አስታውቀዋል፡፡ ያገኘነውን ጥቅም ዘላቂ ለማድረግ ያለማንም ቅስቀሳ በሳምንት ከሁለት ቀናት በላይ ጊዜአቸውን ለተፋሰስ ልማት ዘመቻው እያዋሉ መሆኑን አርሶ አደሩ አስታውቀዋል፡፡ በክልሉ በዘንድሮ ዓመት የበጋ ተፋሰስ ልማት ዘመቻ በአጠቃላይ ከ39 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ለማከናወን መታቀዱን ከቢሮው የተገኘ መረጃ ያሳያል፡፡
ተፈጥሮን መሰረት ያደረገ የአካባቢ ሥነ-ምህዳር ጥበቃ ሥራ ለማስፋት እየተሰራ ነው - ግብርና ሚኒስቴር
Mar 15, 2024 322
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2016 (ኢዜአ)፦ ተፈጥሮን መሰረት ያደረገ የአካባቢ ሥነ-ምህዳር ጥበቃ ሥራ በማስፋት ብዝኃ ሕይወትን በዘላቂነት ለመጠበቅና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ። 32ኛው የኢትዮጵያ ሥነ-ሕይወት ባለሙያዎች ማኅበር ጉባኤ በአዲስ አበባ ተጀምሯል። የግብርና ሚኒስቴር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤልያስ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ መንግሥት የግብርና ምርታማነትን ማስቀጠል የሚያስችሉ አሰራሮችን ተግባራዊ እያደረገ ነው። በሥነ-ምኅዳር ጥበቃና በአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የተከናወኑ ተግባራትም የተራቆተ የመሬት ገጽታን በመመለስ ምርታማነት እንዲጨምር እያደረጉ ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብሩ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ለሥነ-ምኅዳር ጥበቃ አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሥነ-ሕይወት ባለሙያዎች ማኅበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ቢቂላ ወርቅነህ፤ በጉባኤው የሥነ-ምኅዳር ጥበቃ ላይ ያተኮሩ የምርምር ሥራዎች ቀርበው ምክክር እንደተደረገባቸው ገልጸዋል። የምርምር ውጤቶችም ለፖሊሲ አውጪዎች፣ ለአስፈፃሚ አካላትና ለምርምር ተቋማት በግብዓትነት እንዲያገለግሉ ይደረጋል ብለዋል። የምርምር ሥራዎቹም የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የተራቆቱ አካባቢዎችን እንዲያገግሙ በማድረግ የመጣውን ውጤት የሚያስቀጥሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሥነ-ሕይወት ባለሙያዎች ማኅበር ምክትል ፕሬዝዳንት ዶክተር ቤዛወርቅ አፈወርቅ፤ በኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች የደን ሽፋን እንዲጨምር አስችሏል ብለዋል። በኢትዮጵያ የተመዘገበውን ውጤታማ ደን ልማት ለማስቀጠል በጥናትና ምርምር የታገዙ ሥራዎችን ማስፋት እንደሚያስፈልግ ምክረ ሃሳብ ሰጥተዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም ሁነኛ መፍትሔ ነው ያሉት ደግሞ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉ ተመራማሪ ዶክተር ገመዶ ዳሌ ናቸው። በአረንጋዴ አሻራ መርሃ ግብር እየተመዘገበ የመጣውን ውጤት ለማስቀጠል የዘርፉ ተመራማሪዎች አዎንታዊ ሚናቸውን መጫወት እንደሚገባቸው ተናግረዋል። 32ኛው የኢትዮጵያ ሥነ-ሕይወት ባለሙያዎች ማኅበር ጉባኤ ዛሬን ጨምሮ ለሁለት ተካታታይ ቀናት እንደሚካሄድ ተገልጿል።
በበጋ ወራት ያከናወናቸው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የምግብ ዋስትናችንን ለማረጋገጥ ረድተውናል- የጉጂ አርሶ አደሮች
Mar 14, 2024 226
ነገሌ፤ መጋቢት 5/2016(ኢዜአ)፦ በበጋ ወራት ያከናወኗቸው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የምግብ ዋስትናቸውን ለማረጋገጥ እያገዛቸው መሆኑን የጉጂ ዞን አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የዞኑ ህዝብ ባለፉት ሁለት ወራት 72 ሚሊዮን ብር የሚገመት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች መከናወናቸውን አስታውቋል። በዞኑ የድርቅ ተጋላጭነትን በዘላቂ ልማት ለመቋቋም የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጿል፡፡ በአናሶራ ወረዳ የቡልዮ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ሂርባዬ ባሬቶ ባለፈው ዓመት ያካሄዱት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ተስፋ ሰጪ ውጤት እንዳዩበት ተናግረዋል፡፡ በአካባቢያቸው የተከሏቸው ችግኞች በአብዛኛው መጽደቃቸውንና በዘንድሮ የበጋ ወቅት ምንጮች ሳይደርቁ መክረማቸውን አስረድተዋል፡፡ ''ተፋሰሶችን ማልማት፣ ችግኝ መትከልና ተንከባክቦ ማሳደግ ድርቅና የአካባቢ መራቆትን ለመከላከል ብቸኛው አማራጭ እንደሆነ በተግባር አይቻለሁ'' ብለዋል እርሶ አደሩ፡፡ ከዓመታት በፊት በቀበሌ ተገደው ይሰሩት የነበረው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ አሁን በራሳቸው ፍላጎት የሚሰሩት መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ዘንድሮም በተመረጡ ተፋሰሶች ላይ እርከን መስራታቸውን የሚናገሩት አቶ ሂርባዬ፣ በዚህም የተራቆተ የግጦሽ ሳር መሬት መከለላቸውንና የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ማዘጋጀታቸውን ተናግረዋል፡፡ በወረዳው የራያ ቦዳ ቀበሌ ነዋሪው አቶ ገመዳ ሶራ እንዳሉት በአካባቢ መራቆት፣ በዝናብ እጥረትና በድርቅ የእንስሳት መኖ ችግር በተደጋጋሚ ያጋጥማቸዋል፡፡ ከዚህም አልፎ ወንዞችና ምንጮች በመድረቃቸው በቤት እንስሳት ላይ ሳይቀር ቀላል የማይባል ጉዳት ያደርሳል ብለዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ከደረሰብኝ ችግር ትምህርት ወስጄያለሁ የሚሉት አቶ ገመዳ፣ ምንጮችን በማጎልበት፣ በእርከን ሥራና በአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ ዝግጅት ላይ በሳምንት ሶስት ቀናት እየተሳተፉ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ወንዶ ሸርቦቴ በዞኑ ከጥር ወር ጀምሮ እየተካሄደ ባለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች 72 ሚሊዮን ብር የሚገመቱ ተግባራት እንደተከናወኑ አስታውቀዋል። ከሥራዎቹ ከ100 ሺህ ሄክታር በላይ በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ ችግር ምክንያት የተራቆተ መሬት መሸፈኑንና ከ133 ሺህ በላይ የማህበረሰብ ክፍሎች መሳተፋቸውን ገልጸዋል፡፡ እስካሁንም ለአደጋ በተጋለጡ አካባቢዎች የድንጋይ ግንብ ማሰር፣ የእርከንና የግጦሽ መሬትን ከሰውና ከእንስሳት የመከለል ሥራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል፡፡ እንዲሁም 282 ሺህ የችግኝ መትከያና የጎርፍ መከላከያ ጉድጓዶች መዘጋጀታቸውን የገለፁት የቡድን መሪው፣102 ሺህ ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል፡፡
በትግራይ ክልል ከ27 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ተከናውኗል
Mar 12, 2024 251
መጋቢት፤3 ቀን 2016 ዓ.ም (ኢዜአ)፡-በትግራይ ክልል በዘንድሮ በጋ ከ27 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የአፈርና የአካባቢ ጥበቃ ሥራ መከናወኑን የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ግብርናና የተፈጥሮ ሃብት ቢሮ አስታወቀ፡፡ በቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና ምግብ ዋስትና ዘርፍ የተፋሰስ ልማት ዳይሬክተር አቶ ደስታ ገብረስላሴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ከየካቲት 04 ቀን 2016 ዓ/ም ጀምሮ በአርሶ አደሩ የነቃ ተሳትፎ የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው፡፡ በዘንድሮው ነጻ የአፈርና ውሃ ጥበቃ የዘመቻ ሥራ 50 ሺህ ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ እስካሁን ከ27 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የድንጋይና የአፈር እርከን፣ የምንጭና እርጥበት የማጎልበት ሥራዎች ተሰርተዋል ብለዋል፡፡ በክልሉ ተቋርጦ የነበረውን የነጻ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ በአሁኑ ወቅት የተገኘውን ሰላም በመጠቀም በቀን 800 ሺህ የሚሆኑ ነዋሪዎችን በማሳተፍ እንዲቀጥል መደረጉን ገልፀዋል፡፡ በአንድ ሺህ 385 ተፋሰሶች ላይ የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የገለጹት አቶ ደስታ የድርቅ አደጋ ተጋላጭነትን ለመከላከል እና ምርታማነትን ለማሳደግ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ተግባራትን ማጠናከር እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡ በጽራእ ወንበርታ ወረዳ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ የሥራ ሂደት አስተባባሪ አቶ ገብረ እግዚአብሄር ገብረስላሴ በበኩላቸው ለበርካታ ዓመታት በወረዳው በተከናወነ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ሥራ ከሁለት ሺህ በላይ ሄክታር መሬትን በመስኖ የማልማት አቅም እንዲፈጠር ማስቻሉን ገልጸዋል፡፡ በዚህም አርሶ አደሮች ተጠቃሚነታቸውን እያረጋገጡ መሆናቸውን የተናገሩት አስተባባሪው ዘንድሮ በወረዳው ከአንድ ሺህ ሁለት መቶ ሄክታር መሬት በላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ አየተከናወነ ነው ብለዋል፡፡ በወረዳው የሚካኤል አምባ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር ግደይ አባዲ እና ቄስ ዘርአይ ደስታ እንዳሉት፤ የድርቅ ተጋላጭነትን ለመከላከል አርሶ አደሩ በልማት ሥራው እየተሳተፈ ነው፡፡ ባለፉት ዓመታት በተሰሩ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች አረንጓዴ አካባቢ መፈጠሩን ገልፀው የዘንድሮውን የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ስኬታማ ለማድረግ አርሶ አደሩና የግብርና ባለሙያዎች ተቀናጅተው እየሰሩ መሆናቸውን አርሶ አደሮቹ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም በትግራይ ክልል ለዓመታት የተከናወኑ ስኬታማ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች ኢትዮጵያን በዓለም አቀፍ ደረጃ ተሸላሚ እንዳደረጋት የሚታወስ ነው።
በድሬዳዋ ከ5ሺህ 500 ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የአፈርና የውሃ ጥበቃ ስራዎች መከናወናቸው ተገለጸ
Mar 9, 2024 336
ድሬዳዋ ፤ የካቲት 30/2016(ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ አስተዳደር የገጠር ቀበሌዎች ለአንድ ወር በተካሄደ የልማት ዘመቻ ከ5ሺህ 500 ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የአፈርና የውሃ ጥበቃ ስራዎች መከናወናቸው ተገለጸ። በድሬዳዋ ለአንድ ወር በገጠር ቀበሌዎች ሲካሄድ የሰነበተው የተፋሰስ ልማት መጠናቀቁን ተከትሎ በተከናወኑ ስራዎች ላይ ግምገማ ተደርጓል። በዚህ ወቅት እንደተገለጸው፤ ዘንድሮ ለአንድ ወር በ38 የድሬዳዋ ገጠር ቀበሌዎች በህብረተሰቡ ተሳትፎና በግብርና ባለሙያዎች ድጋፍ 5ሺህ 550 ሄክታር መሬት ላይ የአፈርና የውሃ ጥበቃ ስራዎች ተከናውነዋል። ግምገማውን የመሩት የድሬደዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ፤ የገጠሩን የተፈጥሮ ሃብት በዘላቂነት ተንከባክቦ ለመጠቀም በተራቆቱ ተፋሰሶች ላይ የተከናወኑ የልማት ስራዎች አበረታች መሆናቸውን ተናግረዋል። ይህም በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እንደሚያግዝ አመልክተው፤ ስራዎቹ ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አሳስበዋል ። የድሬዳዋ አስተዳደር የግብርና ፣ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኑረዲን አብደላ እንዳሉት፤ ባለፉት ስምንት ዓመታት በህብረተሰቡ ተሳትፎ በተከናወኑ የአፈና የውሃ ጥበቃ ስራዎች የጠፉ የውሃ ምንጮችና ተጨማሪ የእርሻ መሬትን ለልማት ማመቻቸት ተችሏል። በጎርፍና በዝናብ ይጠረግ የነበረ ለም አፈር በመከላከል የአነስተኛ የመስኖ ስራዎች በስፋት እንዲጀመሩ በማድረግ የገጠሩ ህብረተሰብ ተጨማሪ ገቢ እያገኘ መምጣቱን አስረድተዋል። ዘንድሮ በተካሄደው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ ላይ 38 ሺህ የሚጠጉ የገጠር ነዋሪዎች እንደተሳተፉ ጠቅሰው፤ በዚህም 3ሺህ 750 ሄክታር የመስኖ ማሳ ላይ የውሃ አጠቃቀምን ያሻሻሉ ስራዎች ከተከናወኑት ውስጥ እንደሚገኙበት አመልክተዋል። ከግምገማው በኋላም በአስተዳደሩ በሚገኙ አራት የገጠር ክላስተሮች በተፋሰሱ ልማት የተሻለ ስራ አፈፃፀም ላስመዘገቡ ቀበሌዎች የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። ሽልማቱን ያበረከቱት ከንቲባ ከድር ጁሃርና ሌሎች የአስተዳደሩ የአመራር አባላት ናቸው። ተሸላሚ ከሆኑት መካከል አርሶ አደር መሐዲ መሐመድ በሰጡት አስተያየት፤ ፤ባለፉት ዓመታት ያከናወኗቸው የአፈርና የውሃ ጥበቃ ስራዎች ምንጮች እንዲጎለብቱና በአነስተኛ መስኖ እንዲሰማሩ እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። ሌላው ተሸላሚ አርሶአደር ኡስማኢል ዑመር በበኩላቸው ፤ የተፈጥሮ ሃብትን መጠበቅና መንከባከብ ማሳችንን የሚሰጠንን ምርት እንዲጨምር አግዞናል፤ የጠፉ ዕፀዋቶችና የደረቁ ምንጮች ጎልብተዋል ብለዋል። በቀጣይም በፈጠሩት አደረጃጀት ታግዘው የተፋሰስ ልማቱን እንደሚያስቀጥሉ ገልጸዋል ።
ከአካባቢ ብክለት ነፃ የሆነች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የወጡ ህጎች እንዲፈፀሙ ትኩረት ተሰጥቷል
Mar 8, 2024 313
ሀዋሳ ፤ የካቲት 29/2016 (ኢዜአ)፡- ከአካባቢ ብክለት ነፃ የሆነች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በመንግስት የወጡ ህጎች ህዝብን ባሳተፈ አግባብ እንዲፈፀሙ ትኩረት መሰጠቱን የኢትዮዽያ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ገለጸ። አገር አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ የግማሽ በጀት ዓመቱ ዕቅድ አፈፃጸም የግምገማ መድረክ በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ነው። በዚህ ወቅት የኢትዮዽያ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ለሊሴ ነሚ እንዳሉት፤ ዘላቂ ሀገራዊ የኢኮኖሚ እድገት ለማጠናከር ዜጎች ባልተበከለና ንጹህ አካባቢ እንዲኖሩ ማመቻቸት ያስፈልጋል። ለዚህም አረንጓዴ የሆነችና ከብክለት የፀዳች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በመንግሥት የወጡ የአካባቢ ጥበቃ ህጎች ህዝብን ባሳተፈና በተቀናጀ አግባብ እንዲፈፀሙ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። በዚህ ረገድ በግማሽ የበጀት ዓመቱ የአካባቢ ህጎች ተከባሪነት ለማረጋገጥ ክትትልና ቁጥጥር ከማጠናከር ባለፈ በአካባቢ ጉዳዮች ዙሪያ የህብረተሰቡን ግንዛቤ ለማጎልበት ጥረት መደረጉን ጠቅሰዋል። በከተሞች የተቀናጀ ደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ዕቅድ አዘጋጅተው እንዲተገብሩም ድጋፍ መደረጉንም ተናግረዋል። እንዲሁም በበርካታ የማምረቻ ኢንዱስትሪዎችና አገልግሎት መስጫ ተቋማት የቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ በሰውና አካባቢ ላይ ጉዳት አለማስከተሉን ክትትል ተደርጓል ብለዋል። ይህንን ተከትሎ ተቋማቱ የተቀናጀ የቆሻሻ አወጋገድና የኬሚካል አያያዝ እቅድ አዘጋጅተው እንዲተገብሩ በትኩረት መሰራቱን አመልክተዋል። መድረኩም የተዘጋጀው በየአካባቢው የተገኙ ውጤቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠልና ክፍተቶችን ለማስተካከል በቀጣይ በሚሰሩ ተግባራት ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ለማስገንዘብ መሆኑን አስረድተዋል። በመድረኩ የተገኙት የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በበኩላቸው፤ የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል በጋራ መረባረብ እንደሚገባ አመልክተዋል። የተፈጥሮ ሀብቶች መመናመን፣ የደረቅና ፍሳሽ ቆሻሻ በአግባቡ አለመወገድ ተግዳሮትን ለማስቀረት የአንድ ተቋም ጥረት ብቻ ከግብ አያደርስም ብለዋል። የአረንጓዴ ልማትን አጠናክሮ የቆሻሻ አያያዝና አወጋገድን በማዘመን እንዲሁም የወጡ ህጎች እንዲተገበሩ በቅንጅት መረባረብ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። የሲዳማ ክልል ደንና አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሽታዬ ዩሙራ ፤ በክልሉ ለአካባቢ ጥበቃ ትኩረት በመስጠት ለአረንጓዴና ለዘላቂ ልማት መረጋገጥ አበክረው እየሰሩ መሆናቸውን አብራርተዋል። ለሁለት ቀናት በተዘጋጀው የግምገማው መድረክ ከሁሉም ክልሎች የተውጣጡ የዘርፉ የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
በኦሮሚያ ክልል በክረምቱ 500 ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኝ ይተከላል
Mar 8, 2024 248
ሐረር ፤ የካቲት 29 / 2016(ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብር ወቅት ለሰው ምግብነት የሚውል 500 ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኝ እንደሚተከል የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በአገር ደረጃ 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን የተለያየ ዓይነት ችግኝ ለመትከል ታቅዶ እየተሰራ መሆኑም ተመልክቷል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ እንዳሉት፤ በዘንድሮው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተለያየ የችግኝ ዓይነት ለመትከል ከወዲሁ ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል። በክልሉ አጠቃላይ ለመትከል ከታቀደው ችግኝ ውስጥ እስካሁን ከ80 በመቶው በላይ መዘጋጀቱን ጠቅሰው፤ በዋናነት ለፍራፍሬ ችግኝ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። ከፍራፍሬ ችግኙ መካከል አቮካዶ፣አፕል፣ማንጎ፣ብርቱካንና አናናስ እንደሚገኝበት ጠቅሰው፤ ዘንድሮ ለመጀመርያ ጊዜ የቴምር ችግኝ እንደሚተከልና ለዚህ ዝግጅት መደረጉን አስታውቀዋል። በተለይ በዘንድሮው መርሃ ግብር ለሰው ምግብነት የሚሆን 500 ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኝ እንደሚተከል ገልጸዋል። ፍራፍሬን ጨምሮ በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብር የሚተከለው የተለያየ ዓይነት ችግኝ የአካባቢን የአየር ሚዛን ብሎም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራን በማሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡ በክልሉ በበጋ ወቅት እየተከናወነ ያለው የተፋሰስ ልማት ስራ በክረምት ለሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መደላደልን እየፈጠረ ነው ያሉት አቶ ጌቱ፤ ከተፋሰስ ልማቱ በተጓዳኝ ለችግኝ ተከላው የጉድጓድ ዝግጅት መደረጉን ገልጸዋል፡፡ በተለይ በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ጋራ ጊሌ ተፋሰስ ላይ ባለፈው ዓመት የተተከለው ችግኝ ሙሉ በሙሉ ማጽደቅ እንደተቻለ በመስክ ምልከታ መታወቁን የጠቀሱት አቶ ጌቱ፤ በሌሎች አካባቢዎችም ያለው የችግኝ የጽድቀት መጠናቸው አበረታች መሆኑን ተናግረዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤሊያስ በበኩላቸው ፤ ዘንድሮ እንደ አገር 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። እስካሁንም 4 ነጥብ 8 ቢሊዮን ችግኝ መዘጋጀቱንም አመልክተው ፤ ለችግኝ ተከላው ደግሞ 1 ነጥብ 8 ሚሊየን ሄክታር መሬት መሰናዳቱን አስረድተዋል። እንደ ፕሮፌሰር እያሱ ገለጻ ፤ ለችግኝ ተከላው የሚያገለግሉ በበጋ ወራት በአገሪቱ የተፋሰስ ልማት ስራዎች በስፋት ተከናውነዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታውና የክልል ግብርና ቢሮ የአመራር አባላት ሰሞኑን በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ግራዋ ወረዳ በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ የተከናወኑ ስራዎችን ተዘዋውረው መመልከታቸውን በወቅቱ ተገልጿል።
በምስራቅ ሐረርጌ ዞን የተከናወኑ ስኬታማ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች የህዝቡ ቁርጠኝነት የታየበት መሆኑ ተገለጸ
Mar 4, 2024 342
ሐረር ፤ የካቲት 25/2016 (ኢዜአ)፡ - በምስራቅ ሐረርጌ ዞን የተከናወኑ ስኬታማ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች የህዝብ ቁርጠኝነት የታየበትና ተሞክሮው ሊስፋፋ የሚገባ ነው ሲሉ የተለያዩ የክልል ግብርና ቢሮ ሃላፊዎች ተናገሩ። የክልል ግብርና ቢሮ የስራ ኃላፊዎች ይህን የተናገሩት በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ግራዋ ወረዳ በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ የተከናወኑ የልማት ስራዎችን በጎበኙበት ወቅት ነው። የሲዳማ ክልል የእርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ፍቅረየሱስ አሸናፊ እንደተናገሩት በዞኑ የተከናወኑ የተፋሰስ እና የተፈጥሮ ሃበትና ልማት ጥበቃ ስራዎች ህዝብ ሲተጋና በቁርጠኝነት ሲሰራ ሁሉንም ማከናወን እንደሚቻል በተግባር የተመለከቱበት ነው። በተለይ አርሶ አደሩና ማህበረሰቡ ያከናወኑት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራን የህልውና ጉዳይ አድርገው የወሰዱበት መሆኑን ይገልጻል ብለዋል። በወረዳው ባለፉት ዓመታት በተፋሰሶች ላይ የተከናወኑት የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች ወደ ለምነት መቀየራቸው፣ የደረቁ ምንጮች በመመለሳቸው እና ለወጣቶች የስራ እድል ፈጥሮ መመልከታቸውን ገልጸዋል። በዞኑ የተከናወኑ አበረታች የተፋሰስ ልማት እና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ተሞክሮን ወደ ክልሉ ለማስፋፋት ይሰራል ብለዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በስነ-ህይወታዊ ዘዴ የማጠናከርና ከሌሎች የሰብል ልማት፣ እንስሳት እርባታ እንዲሁም ከአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ጋር አያይዘው ያከናወኑት የተቀናጁ የግብርና ልማት ስራ አበረታች መሆኑን የተናገሩት በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአማራ ክልል ገጠር ልማት አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ሃላፊ ዶክተር ድረስ ሳህሉ ናቸው። አሁንም በዞኑ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ በህዝብ ንቅናቄና በይቻላል መንፈስ በስፋት እየተከናወነና መሬቱም ለግብርና ልማት ስራ እንዲውል እየተደረገ እንደሚገኝ መመልከታቸውን ተናግረዋል። የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራን በጥራት ማከናወን እንደሚቻልና በስፍራውም የተቀናጀ የግብርና ልማትን በማከናወን ተጠቃሚ መሆን እንደሚቻል መመልከታቸውነና መነሳሳትንም የፈጠረ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ የተመለከቷቸው ነባርና አዲስ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ልምድ ሊወሰድበትና ሊስፋፋ የሚገባው መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮዽያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ውብሸት ዘነበ ናቸው። በተለይ በለሙ በተፋሰሶች ላይ የተከናወኑት የንብ ማነብ፣ የከብት እርባታና ሌሎች የግብርና ልማት ስራዎች የአካባቢው ማህበረሰብ የኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆን ማስቻሉንና ትምህርት የተገኘበት እንደሆነም አመልክተዋል። የምስራቅ ሐረርጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ሚስኪ መሀመድ በበኩላቸው በዞኑ በተከናወነው የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች ውጤታማ ናቸው ብለዋል። በተለይ ባለፉት ሶስት ዓመታት በአመራሩ፤ ማህበረሰቡና የግብርና ባለሞያው ተቀናጅቶ ባከናወነው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ አካባቢው ወደ ለምነት ከመቀየሩ ባለፈ በርካታ ወጣቶች የስራ እድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማስቻሉን ተናግረዋል። በዞኑ የተከናወነው የተፈጥሮ ሃበት ጥበቃ ስራ ተስፋ ሰጪና ለሌሎችም እንደ ተሞክሮ እየተወሰደና እየተስፋፋ ይገኛል ሲሉ ገልጸዋል። በምስራቅ ሐረርጌ ዞን በዘንድሮ የበጋ ወቅት በ477 ተፋሰሶች ላይ የተለያዩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች ተከናውነዋል።
የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ በግብርናው ዘርፍ ለሚከናወኑ የልማት ስራዎች ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል- ፕሮፌሰር እያሱ ኤሊያስ
Mar 3, 2024 287
ሐረር ፤ የካቲት 24 / 2016 (ኢዜአ) ፡- የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ተግባር በግብርናው ዘርፍ ለሚከናወኑት የልማት ስራዎች ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤሊያስ ገለጹ። የግብርና ሚኒስቴርና የክልል ግብርና ቢሮ የስራ ኃላፊዎች በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ግራዋ ወረዳ በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ የተከናወኑ የልማት ስራዎችን ተመልክተዋል። በዚህ ወቅት ፕሮፌሰር እያሱ ኤልያስ እንደተናገሩት ባለፉት ዓመታት በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ የተከናወኑ ተግባራት በግብርናው ዘርፍ ላይ ተጨባጭ ውጤት እንዲገኝ አስተዋጽኦ አድርገዋል። በተለይ በንብ ማነብ፣በከብት እርባታና ማድለብ ፣በሌማት ቱሩፋት እንዲሁም በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት፣ በአረንጓዴ አሻራና በሌሎች የግብርና ዘርፎች ለውጥ እንዲመጣ ያበረከተው አስተዋጽኦን ጠቅሰዋል። በአገሪቱ በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ የሚከናወኑ ተግባራት ይደርሱ የነበሩ የጎርፍ አደጋዎች እንዲቀንሱ ከማስቻሉ ባለፈ አካባቢዎች አረንጓዴ እንዲላበስና ምግብ ዋስትና እንዲረጋገጥ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል። በተለይ በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ግራዋ ወረዳ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑት የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች የግብርና ልማት ስራዎችን ከማሳለጥ ባለፈ ወጣቶች በተለያየ መልኩ የስራ እድል እንዲያገኙ ማስቻሉን እንደተረዱም አውስተዋል። በሐምሌ ወር 2015 ዓም በወረዳው “ጋራ ጊሌ” ተፋሰስ ላይ የተተከሉ የአትክልትና ሌሎች ችግኞች ሙሉ በሙሉ እንደፀደቁ መመልከታቸውን ጠቅሰዋል። ዘንድሮም በወረዳ “አበል ቃሲም” ሌሎች ተፋሰሶች ላይ ከጥር አጋማሽ ጀምሮ ህብረተሰቡ በነቂስ ወጥቶ ያከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች ለተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና ምርታማነትን ለማሳደግ ፋይዳው የጎላ መሆኑን እንደተረዱም ፕሮፌሰር እያሱ አመላክተዋል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ ጌቱ ገመቹ በበኩላቸው፤ ቢሮው ለተፋሰስ ልማት ስራዎች ትኩረት በመስጠት እየደገፈ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም በክልሉ የሚከናወኑ የግብርና ስራዎች በትክክለኛው መንገድ እንዲሄዱ አስችሏል ያሉት ሃላፊው፤ በዚህም በየዓመቱ በተፋሰሶች የሚለማው መሬት ስፋት እየጨመረ መምጣቱን አመልክተዋል። ዘንድሮም የተፋሰስ ልማት ትግበራን በማስቀጠል የእርከንና ክትር ጨምሮ የተለያዩ የአፈርና ውሃ ዕቀባ ስራዎች ሲከናወኑ እንደቆየ አውስተዋል። በተለይ ባለፈው ዓመት በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ግራዋ ወረዳ ጋራ ጊሌ ተፋሰስ ላይ የተከናወነው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ በአካባቢው የጠፉትን ምንጮች ጎልብተው የዓሳ ልማት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። በተፈጥሮ ሀብት ልማትና እንክብካቤ ስራው የተራቆተው መሬት አገግሞ በደን መሸፈኑን የገለጹት አቶ ጌቱ፤ በአሁኑ ወቅትም ማህበረሰቡ ንብ በማነብና በእንስሳት መኖ ልማት ተሰማርተው ውጤታማ በመሆን ላይ እንደሚገኝ መታየቱን ተናግረዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ተግባራት በርካታ የተራቆቱ ስፍራዎች ወደ ለምነት እንዲቀየሩ ማስቻሉን የገለጹት ደግሞ የምስራቅ ሐረርጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ሚስኪ መሐመድ ናቸው። የከርሰ ምድር ውሃ እንዲጨምር፣የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት እንዲጎለብትና ምርታማነት እንዲጨምር ማገዙን ገልጸዋል። በምስራቅ ሐረርጌ ዞን በዘንድሮ የበጋ ወቅት በ477 ተፋሰሶች ላይ የተለያዩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች መከናወናቸውንም ወይዘሮ ሚስኪ ተናግረዋል።
አዲሱ የደን ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ደንብ የኢትዮጵያ የካርበን ሽያጭ በህግ እንዲመራ የሚያደርግ ነው
Mar 3, 2024 298
አዲስ አበባ፤ የካቲት 24/2016(ኢዜአ)፦ አዲሱ የደን ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ደንብ የኢትዮጵያ የካርበን ሽያጭ በህግ እንዲመራ የሚያደርግና የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ የሚያሳድግ መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ገለጹ። የሚኒስትሮች ምክር ቤት በ27ኛ መደበኛ ስብሳባው ላይ ተወያይቶ እንዲጸድቅ ውሳኔ ካሳለፈባቸው የህግ ማዕቀፎች መካከል አንዱ "የደን ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም ረቂቅ ደንብ" ነው። ደንቡም ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ በመገንባት የካርቦን ክምችትን በዓለም አቀፉ ግብይት በማስገባት የኢትዮጵያን የደን ሃብት ለማልማትና ለመጠበቅ የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው ከፍተኛ የደን ባለሙያዎች፤ የኢትዮጵያ የደን ሃብት በሚገባ በማልማት የካርቦን ሽያጭ ገቢዋን በማሳደግ ረገድ አዲሱ ረቂቅ ደንብ ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብለዋል። በኢትዮጵያ ደን ልማት የብሔራዊ ‘’ሬድ ፕላስ’’ ፕሮግራም አስተባባሪ ይተብቱ ሞገስ (ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ የካርበን ሽያጭ ማከናወን የሚያስችል የህግ ማዕቀፍ እስካሁን እንዳልነበራት ገልጸዋል። በመሆኑም የሚኒስትሮች ምክር ቤት በ27ኛ መደበኛ ስብሳባው ያጸደቀው የደን ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ደንብ የደን ልማት፣ አጠቃቀምና የካርበን ሽያጭ የህጋዊነት ጥያቄን ምላሽ የሰጠ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ የደን ሃብቷን በማልማት ከዘርፉ የሚገባትን ገቢ እንድታገኝና በህጋዊነት ላይ የነበረውን የአሰራር ክፍተት ምላሽ የሰጠ መሆኑንም አብራርተዋል። የኢትዮጵያ ደን ልማት ከፍተኛ የደን ባለሙያና የአገር አቀፉ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር)፤ በደን ልማት ላይ የመጣውን ተጨባጭ ውጤት በደንብና ህጋዊ የአሰራር ሥርዓት መምራት ተገቢ መሆኑን ገልጸዋል። የዘርፉን ልማት በማሳለጥ የአርሶ እና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሳለጥ እንዲሁም የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ለማሳደግ አዲሱ ደንብ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰዋል። የሚኒስትሮች ምክር ቤት ያጸደቀው የደን ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም ረቂቅ ደንብ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውል ውሳኔ መተላለፉ የሚታወስ ነው።
የግብርና ሚኒስቴርና የክልል ግብርና ቢሮ የስራ ኃላፊዎች በምስራቅ ሐረርጌ ዞን በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የተከናወኑ ተግባራትን እየጎበኙ ነው
Mar 2, 2024 284
ሀረር፤ የካቲት 23/2016(ኢዜአ)፦ የግብርና ሚኒስቴርና የክልል ግብርና ቢሮ የስራ ኃላፊዎች በምስራቅ ሐረርጌ ዞን ግራዋ ወረዳ በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የተከናወኑ ተግባራትን እየጎበኙ ነው። በጉብኝቱ ላይ የግብርና ሚኒስትር ድኤታው ፕሮፌሰር እያሱ ኤልያስን ጨምሮ የተለያዩ ክልሎች የግብርና ቢሮ ኃላፊዎችና የተፈጥሮ ኃብት ጥበቃ ዘርፍ አስተባባሪዎች ተገኝተዋል። የአመራር አባላቱ በዞኑ ግራዋ ወረዳ በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ጋር ተያይዞ የአካባቢው ነዋሪዎች በማር ምርት፣ በእንስሳት እርባታና ማድለብ እንዲሁም በአሳ ሃብት ልማትና በተፈጥሮ ማዳበርያ ዝግጅት ረገድ የተከናወኑ የልማት ሥራዎችን እየጎበኙ ይገኛሉ። የምስራቅ ሀረርጌ ዞን ግራዋ ወረዳ በዚህ ዓመት በተፋሰስ ልማትና በአካባቢ ጥበቃ ስራዎች የተሻለ ስራ ከተከናወነባቸው ስፍራዎች አንዱ መሆኑ ተገልጿል። አሁን ላይ በወረዳው በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ በለማው 'ጋራ ጊሌ' ተፋሰስ ላይ የተከናወኑ የተለያዩ የልማት ስራዎችን በመጎብኘት በልማቱ የተሳተፉ ወጣቶችን አበረታተዋል።
የተፋሰስ ልማት የድርቅ ተጋላጭነታችንን ለመቀነስ እያገዘን በመሆኑ ልማቱን እናጠናክራለን - የምሥራቅ ባሌ ዞን አርሶ አደሮች
Mar 2, 2024 153
ሮቤ ፤ የካቲት 23/2016(ኢዜአ)፦ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የድርቅ ተጋላጭነትን በመቀነስ ረገድ እያገዛቸው በመሆኑ ልማቱን አጠናክረው መቀጠላቸውን በምሥራቅ ባሌ ዞን የጊኒርና ለገሂዳ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ። በዞኑ ዘንድሮ 77 ሺህ ሄክታር መሬትን የሚያካልል የተቀናጀ የተፈጥሮ ኃብት ልማት ሥራ በተቀናጀ ሁኔታ መቀጠሉን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገልጿል። ልማቱ እንደየ አካባቢው ስነ-ምህዳር ለሁለት ወራት የሚቆይ ሲሆን፣ ከ155 በሚበልጡ ተፋሰሶችን ተከትሎ እየለማ መሆኑም ተገልጿል። በሥራው የተሳተፉ የወረዳዎቹ አርሶና ከፊል አርብቶ አደሮች ባለፉት ዓመታት ያከናወኗቸው የተፋሰስ ልማት ሥራዎች በተደጋጋሚ የሚያጋጥማቸውን ድርቅ ለመቋቋም እንደረዳቸው ተናግረዋል። የጊኒር ወረዳው ነዋሪ አርሶ አደር በከር አህመድ እንዳሉት በተፋሰስ ልማት ሥራ የሚከናወኑ የእርከን፣ የጉድጓድና መሰል የልማት ሥራዎች የአፈር መከላትና መሸርሸርን በመቀነስ ውጤት እያስገኘ ነው። በዚህም የተራቆቱ ሥፍራዎች ውሃ መቋጠር መጀመራቸውን ተከትሎ ውሃውን ለግብርና ልማት ሥራ በማዋል ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአካባቢያቸው ደኖች በመጨፍጨፋቸው መሬቱ ገላጣ በመሆን ለአፈር መሸርሸር ተጋልጠው መቆየታቸውን የገለጹት ደግሞ ሌላው የጊኒር ወረዳ የልማቱ ተሳታፊ አርሶ አደር አብዮት መንግስቱ ናቸው። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ ከእንስሳት ንክኪ የተከለሉ አካባቢዎች መልሰው በማገገማቸው ለልማት እየዋሉ መምጣታቸው መነሳሳትን እንደፈጠረባቸው ገልጸዋል። በተያዘው ዓመት የእርከን ሥራን ጨምሮ የተለያዩ የስነ አካላዊ ሥራዎችን ከአካባቢው ማህበረሰብ ጋር በነቂስ ወጥተው እያከናወኑ መሆናቸውን አስታውቀዋል። "አካባቢያቸው ቆላማና ለድርቅ ተጋላጭ በመሆኑ በየዓመቱ የተፋሰስ ልማት ሥራ ማከናወን ግዴታ ነው" ያሉት ደግሞ የለገሂዳ ወረዳ ከፊል አርሶ አደር ኡመር ጣሃ ናቸው። ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የአፈር መሸርሸር በመቀነስ ከልማት ውጭ የነበሩ የግጦሽና የእርሻ መሬት ወደ ልማት በመመለስ ተጠቃሚ እንዳደረጓቸው ገልጸዋል። በተለይ የጎርፍና የአፈር መከላትን በማስቀረታቸው ተመናምኖ የነበረው የተፈጥሮ ደን እያገገመ በመምጣቱ የድርቅ ተጋላጭነታችን በመቀነስ እያገዘን ነው ብለዋል። የጊኒር ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሁሴን ኡመር በበኩላቸው በወረዳው ባለፉት ዓመታት በተከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ጎርፍና የአፈር መሸርሸር እየቀነሰ መጥቷል። "ይህም ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ ባገገሙ መሬቶች ላይ ወጣቶችን በማደራጀት በንብ ማነብና ሌሎች የግብርና ልማት ሥራዎች እንዲገቡ እድል ፈጥሯል''ሲሉም ተናግረዋል። እንደ አቶ ሁሴን ገለጻ፣ በተያዘው ዓመት በወረዳው ከ20ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች በህብረተሰቡ ተሳትፎ እየተካሄደ ነው። የምሥራቅ ባሌ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዘላለም አለማየሁ በበኩላቸው፣ በዞኑ ዘንድሮ 77ሺህ ሄክታር መሬትን የሚያካልል የተቀናጀ የተፈጥሮ ኃብት ልማት ሥራ በዘመቻ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በዘመቻውም ከ365ሺህ በላይ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች እየተሳተፉ መሆናቸውንም ተናግረዋል። በዘመቻው እስካሁን በ65 ሺህ ሄክታር ላይ 30 ሺህ ኪሎ ሜትር እርከን፣ 20 ሺህ ሜትር ኪዩብ ውኃን የሚያስተላልፉ ስትራክቸሮች፣ ከ170 ሺህ የሚበልጡ ውኃን የሚያቁሩ ስትራክቸሮች መሰራታቸውን አስታውቀዋል። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ የአርሶ አደሩን ምርታማነት ከማሻሻል በተጓዳኝ በዞኑ ቆላማ የአርብቶ አደር ወረዳዎች በተደጋጋሚ የሚያጋጥመውን ድርቅ ለመቋቋም እንደሚያግዝም አስረድተዋል። በኦሮሚያ ክልል ዘንድሮ ከ3 ነጥብ 3 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ የተፋሰስ ልማት፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ለማከናወን መታቀዱን የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ መረጃ ያመለክታል። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራው የአርሶ አደሩን ምርታማነት ከማሻሻል በተጓዳኝ፣ በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት ያለመ መሆኑም ተመላክቷል።
በ75 ሚሊዮን ዩሮ የሚተገበር አገር አቀፍ የተቀናጀ የውሃ ሀብት አስተዳደር ፕሮጀክት ይፋ ሆነ
Mar 1, 2024 174
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2016(ኢዜአ)፦ በ75 ሚሊዮን ዩሮ የሚተገበር አገር አቀፍ የተቀናጀ የውሃ ሀብት አስተዳደር ፕሮጀክት ይፋ ሆነ ። ፕሮጀክቱ በጣሊያንና ኔዘርላንድ እንዲሁም በአውሮፓ ህብረት የፋይናንስ ድጋፍ የሚተገበር ሲሆን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴርን ጨምሮ የግብርና፣የጤና፣የትምህርት፣የፕላንና ልማት ሚኒስትሮች እንዲሁም የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በተቀናጀ መልኩ ይተገብሩታል ተብሏል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታው አብርሃም አዱኛ(ዶ/ር) ኢትዮጵያ ያላትን የውሃ ሃብት በአግባቡ ተጠቅማ ለዘላቂ ልማትና ዕድገት እንድታውል የተፋሰስ አካባቢዎችን ማልማት እንደሚገባ ነው የገለጹት። የውሃ ሃብትን ከብክለትና ከብክነት ተከላክሎ በተቀናጀ መልኩ ጥቅም ላይ ለማዋልና አደጋዎችን ለመቀነስ ተፋሰስ ልማት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል። የጣሊያንና የኔዘርላንድ መንግስታት ለኢትዮጵያ የተቀናጀ የውሃ ሃብት አስተዳደር እንዲኖር የገንዘብና የቴክኒክ ድጋፍ እያደረጉ መሆኑን ገልጸው፤ መንግስት የአጋር አካላት ድጋፍ ያልተገኘባቸው ቦታዎች ላይ ትኩረት አድርጎ እንደሚሰራ አመልክተዋል። ዛሬ ይፋ የሆነውና ለአምስት ዓመታት ይተገበራል የተባለው አገርአቀፍ የተቀናጀ የውሃ ሃብት አስተዳደር ፕሮጀክትም ተፋሰሱን በማልማት የውሃ ሃብትን በአግባቡ ለመጠቀም የሚያስችል መሆኑን ጠቁመዋል። ፕሮጀክቱ በአዋሽ፣ አባይ፣ ኦሞ ጊቤ፣ ተከዜ፣ ዋቢ ሸበሌና በዳናኪል ተፋሰሶችን በማልማት የውሃ ሃብትን በአግባቡ ለመጠቀም የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የውሃና መሬት ሃብት ማዕከል ዳይሬክተር ጌቴ ዘለቀ (ዶ/ር) በበኩላቸው ኢትዮጵያ ተፈጥሮ ያጎናጸፈቻትን የውሃ ሃብት በአግባቡ ተጠቅማ ለዘላቂ ልማት እንዳታውል በርካታ እንቅፋቶች መኖራቸውን ተናግረዋል። አገሪቱ ከዝናብ ከምታገኘው ውሃ 40 በመቶ የሚሆነውን በጎርፍ እንደምታጣና ይህን የውሃ ብክነት መሆኑን ጠቅሰዋል። በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚከሰቱ ጎርፍና ድርቅን የመሳሰሉ የተፈጥሮ አደጋዎችን ለመከላከል የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸውና ለዚህ ደግሞ የተቀናጀ አሰራር እንደሚያስፈልግም ነው የገለጹት። ውሃን በአግባቡ በመያዝ ለልማት ማዋል የሚቻለው ዕውቀት መር የሆኑ ስራዎችን በመስራትና ተፋሰሶችን ማልማት ሲቻል መሆኑንም አንስተዋል። በፕሮጀክቱ ይፋ ማድረጊያ መርሀ-ግብር ላይ የተገኙት በኢትዮጵያ የኔዘርላንድ አምባሳደር በኢትዮጵያ የጣሊያን ኤምባሲ የልማትና ትብብር ሃላፊ እንዲሁም የአውሮፓ ህብረት ተወካዮች ኢትዮጵያ የውሃ ሃብቷን በአግባቡ ተጠቅማ ለዘላቂ ልማቷ እንድታውል ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
ኢንስቲትዩቱ የአየር ትንበያ መረጃ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ለመስጠት ጠንካራ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው
Feb 29, 2024 195
ጅማ፤ የካቲት 21/2016(ኢዜአ):-የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የአየር ትንበያ መረጃ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ ለመስጠት ጠንካራ እንቅስቃሴ እያደረገ መሆኑን ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ በጅማ ከተማ በ30 ሚሊዮን ብር ወጪ ያስገነባው የምዕራብ ኦሮሚያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የምርምር ማዕከል ተመርቋል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደተናገሩት ኢንስቲትዩቱ የአየር ጸባይ መረጃን ሰብስቦ በመስጠት ህይወትና ንብረትን ከአደጋ የመጠበቅ ስራ እያከናወነ ነው ። ኢንስቲትዩቱ በተለይም ለግብርናው ዘርፍ ልማት አስተዋጽኦ ሲያበረክት መቆየቱን ገልጸው፣ በአቪዬሽን ሚቲዎሮሎጂና በሌሎችም ዘርፎች ድርሻውን በመወጣት ላይ ይገኛል ብለዋል። ተቋሙ የሚሰበስባቸውን የአየር ትንበያ መረጃዎች ለፖሊሲ አውጪዎችና ለሚመለከታቸው አካላት በማቅረብም ኃላፊነቱን እየተወጣ መሆኑንም አቶ ፈጠነ አስታውቀዋል። ኢንስቲትዩቱ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ አስተማማኝ መረጃ ለመስጠት በጅማ፣ በጅግጅጋ፣ በሐዋሳ፣ በባህር ዳርና በጋምቤላ ከተሞች ማዕከላት እንዳሉት ገልጸዋል። ጅማና አካባቢው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ባላቸው የግብርና ልማት የሚታወቅ በመሆኑ የግብርና ልማትን የአየር ጸባይ ትንበያ መሠረት ባደረገ አገልግሎት ለማጎልበት ጥረት እንደሚደረግ ዋና ዳይሬክተሩ አረጋግጠዋል። በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር አማካሪው አቶ ሞቱማ መቃሳ የአየር ጸባይ ለውጥ ዓለምን እየፈተነ ያለ ጉዳይ መሆኑን ገልጸው፣በአየር ጸባይ ለውጥ የሚከሰቱ ችግሮችን ለመቋቋም አንደኛው መንገድ ትክክለኛና ወቅታዊ መረጃ መስጠት እንደሆነ አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የሚሰጠውን መረጃ መጠቀም ጎርፍና ድርቅን የመሰሉ የተፈጥሮ አደጋዎችን ለመከላከል ዓይነተኛ አስተዋጽኦ እንዳላቸው ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የምእራብ ኦሮሚያ ሚቲዎሮሎጂ ምርምር ማዕከል ሥራ አስፈጻሚ አቶ ገመቹ ራጋ ማዕከሉ በአካባቢው ግብርናና ኢንዱስትሪ ዕድገት አስተዋጽኦ ለማበርከት እንደሚያስችለው ተናግረዋል። ሰባት ጣቢያዎችን የሚያስተዳድረው ማዕከል ከተለያዩ ተቋማት ጋር በቅንጅትና በጋራ እንደሚሰራም አስታውቀዋል። ለማዕከሉ የሚያገለግለው ህንጻ በስምንት ወራት ጊዜ ውስጥ ግንባታው መጠናቀቁ በዚሁ ጊዜ ተገልጿል። በሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙ የተለያዩ ተቋማት ተወካዮችም ማዕከሉን ጎብኝተዋል ።
ኢትዮጵያ ለደን ልማት የሰጠችው ትኩረት ከካርቦን ሽያጭ የምታገኘው ገቢ እንዲጨምር አድርጓል
Feb 28, 2024 167
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2016 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ለደን ልማት የሰጠችው ትኩረት ከካርቦን ሽያጭ የምታገኘው ገቢ እንዲጨምር ማድረጉን የዘርፉ ባለሙያዎች ገለጹ። በኢትዮጵያ የደን ልማት ከአጠቃላይ አገራዊ የምርት መጠን የ13 በመቶ ድርሻ እንዳለው በቅርቡ የተደረገ አገር አቀፍ ጥናት ያመለክታል። ደንና እጽዋት ላይ የተመሰረተ ልማት የአካባቢ መራቆትን ለመከላከል፣ የግድቦችን ውሃ የመያዝ አቅም ለመጨመርና ለመስኖ ስራ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር ትልቅ ድርሻ አለው፡፡ ከዚህ ባለፈ ከደን ልማት የሚገኘው ጥቅም ለአገሪቷ ምጣኔ ሃብታዊ ዕድገት ጉልህ ሚና እያበረከተ መሆኑን ነው የዘርፉ ባለሙያዎች የሚናገሩት። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉ የደን ልማት ከፍተኛ ባለሙያዎች ተመናምኖ የነበረውን የደን ሽፋን ለማሳደግ በተደረጉ ጥረቶች አሁን ላይ የደን ሽፋኑ 17 በመቶ መድረስ መቻሉን አስታውቀዋል። በተለይም የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር ለአገሪቷ ደን ሽፋን መጨመር፣ለብዝሃ ህይወት መበራከትና የካርበን ልቀትን ለመቀነስ ጉልህ ድርሻ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የደን ልማት ከራሷ አልፎ አለም እየተፈተነበት ላለው የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ መፍትሄ እየሰጠ መሆኑን ነው ባለሙያዎቹ የገለጹት። አለም አቀፉ ማህበረሰብ ለኢትዮጵያ የደን ልማት ዕውቅና ከመስጠት ባለፈ በተጨባጭ ለተገኘው ውጤት የሚከፍለው ክፍያ እየጨመረ መምጣቱንም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ደን ልማት ባለሙያና የአገር አቀፉ አረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) እንደሚሉት የደን ልማት ለስነምህዳር መሻሻል ካለው ጠቀሜታ ባለፈ አገሪቷ ከካርቦን ሽያጭ ገቢ እንድታገኝ አስችሏታል። አገራት የኢትዮጵያን የደን ልማት ስራዎች በተጨባጭ በመፈተሽ ተገቢውን ክፍያ እየፈጸሙ መሆኑንም ነው ያነሱት። በኢትዮጵያ ደን ልማት ብሔራዊ የ”ሬድ ፕላስ” ፕሮግራም አስተባባሪ ይተብቱ ሞገስ (ዶ/ር) በበኩላቸው ኢትዮጵያ ከደን ልማት ብቻ በአመት ግማሽ ቢሊዮን ዶላር የማግኘት ዕድል እንዳላት ነው ያነሱት። ያደጉት አገራት ለአየር ብክለት ያላቸው ድርሻ የጎላ መሆኑን ጠቅሰው፣ ይህን ለማካካስ በታዳጊ አገራት ደን በማልማት የካርቦንዳይኦክሳይድ ጋዝን ከከባቢ አየር ለመቀነስ ጥረት እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የተራቆቱ አካባቢዎችን በደን በመሸፈንና ደን በማልማት ወደ ከባቢ አየር የሚገባን የተበከለ አየር በመቀነስ ሃላፊነቷን በአግባቡ እየተወጣች መሆኑንም ነው ያስረዱት። ከካርቦን ሽያጭ የሚገኘው ክፍያ ለተጨማሪ የደን ልማትና አካባቢ ጥበቃ ስራዎች የሚውል መሆኑንም ነው ባለሙያዎቹ ያነሱት። የካርበን ሽያጭ ክፍያ ደንን ከጭፍጨፋ በመከላከልና በማልማት የካርበን ልቀትን በመቀነስ ለሚከናወነው ሥራ የሚከፈል ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ደን ልማት ዕውቅና ከሰጡ አጋር አገራት ኖርዌይ አንዷ ናት። ኖርዌይ ኢትዮጵያ በደን ልማት ዘርፉ እያከናወነች ላለው ስራ የ75 ሚሊዮን ዶላር ክፍያ ለመፈጸም ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ስምምነት መፈረሟ ይታወሳል።
ባላፉት ሰባት ወራት ከ500 ሺህ በላይ የተሻሻሉ ማገዶ ቆጣቢ ቴክኖሎጂዎች ለተጠቃሚዎች ተከፋፍለዋል
Feb 28, 2024 187
አዳማ ፤ የካቲት 20/2016(ኢዜአ)፦ ባላፉት ሰባት ወራት ከ500 ሺህ በላይ የተሻሻሉ ማገዶ ቆጣቢ ቴክኖሎጂዎችን በማሰራጨት የታዳሽ ሃይል አጠቃቀምን በገጠር አካባቢዎች የማላመድ ስራ ተጠናክሮ መቀጠሉን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የገጠር ኢነርጂ ቴክኖሎጂ ልማትና ሽግግር መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ ብርሃኑ ወልዱ ለኢዜአ እንደገለፁት ከዋናው የኤሌክትሪክ ማሰራጫ ርቀው የሚገኙ የገጠር አካባቢዎችን በታዳሽ ሃይል ተጠቃሚ የማድረግ ስራ እየተሰራ ነው። በዘንድሮው ዓመት አንድ ሚሊዮን የተሻሻሉ ማገዶ ቆጣቢ ቴክኖሎጂዎችን ለማከፋፈል ታቅዶ፤ ባለፉት ሰባት ወራት ከ500 ሺህ በላይ ማሰራጨት ተችሏል ብለዋል፡፡ በዚህም የአየር ንብረት መዛባትን፣ የአካባቢ ብክለትንና የማገዶ ፍጆታን በመቀነስ በገጠር አካባቢዎች የታዳሽ ሃይል አጠቃቀምን የማላመድ ስራው ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል፡፡ የአካባቢን ስነምህዳር የሚያውኩ በካይ ጋዞችን ከመቀነስ አኳያም አስተዋጽኦው የጎላ መሆኑን ስራ አስፈፃሚው ገልፀዋል፡፡ አክለውም ከሶስት ሺህ በላይ የባዮ ጋዝ ማብላያዎች በገጠሪቱ ኢትዮጵያ መገንባታቸውን ጠቁመው፤ ከባዮጋዝ የሚወጣው ተረፈ ምርትም ለማዳበሪያነት ከፍተኛ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ አያይዘውም ከ250 ሺህ በላይ የገጠር ቤቶች ከውጭ በመጡ የሶላር ቴክኖሎጂዎች ብርሃን እያገኙ መሆኑን የገለጹት አቶ ብርሃኑ፤ በቅርቡ የተጠናቀቁ ከ12 በላይ የሀገር ውስጥ የሶላር ፕሮጀክቶችም ማህበረሰቡን ማገልገል መጀመራቸውንም አክለዋል፡፡ በገጠር አካባቢ ያለው የታዳሽ ሃይል ተደራሽነትና ተጠቃሚነት በአማራና ደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምርጥ ተሞክሮ የታየባቸውን አካባቢዎች በክላስተር በማደራጀት የማስፋፋት ስራ እየሰሩ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል፡፡ የኤሌክትክ ሃይል ስርጭት በማይደርስባቸው አካባቢዎች ባዮ ጋዝ፣ ማገዶ ቆጣቢና የሶላር ቴክኖሎጂን በስፋት ጥቅም ላይ በማዋል ለውጥ እየተገኘ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ወይዘሮ ወይኒቱ ገዳለ ናቸው፡፡ በተለይም ባዮጋዝና ማገዶ ቆጣቢ ቴክኖሎጂዎችን በማስፋፋት ምርጥ ተሞክሮ የታየባቸውን አካባቢዎች በክላስተር በማደራጀት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዚህም በርካታ የገጠሪቷ አካባቢዎች በቴክኖሎጂውና በበሶላር ሃይሉ ብርሃን እያገኙ መሆናቸውን በማከል። የአማራ ክልል ውሃና ኢነርጂ ቢሮ ህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ወይዘሮ መሰለች ዘላለም በበኩላቸው፤ በክልሉ የነበረውን የሃይል እጥረት ችግርና ተያያዥ ችግሮችን በዚሁ ቴክኖሎጂ በመታገዝ እየፈቱ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ባዮጋዝን በመጠቀም በእንጨት ሰበራ ሰበብ የሚባክን የተማሪዎች ጊዜና ጉልበት ብሎም ለአደጋ ተጋላጭነት መቀነስ መቻሉንም ጠቁመዋል፡፡
ኖርዌይ ኢትዮጵያ በደን ልማት እያከናወነች ላለው ስራ የ75 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ አደረገች
Feb 27, 2024 235
አዲስ አበባ፤ የካቲት 19/2016(ኢዜአ)፦ ኖርዌይ ኢትዮጵያ በደን ልማት እያከናወነች ላለው ስራ የ75 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ አደረገች። ድጋፉ ደንን በዘላቂነት በማልማት ወደ ከባቢ አየር የሚገባውን በካይ ጋዝ ልቀትን ለመቀነስ እያከናወነች ያለውን ስራ ለማበረታታት የተደረገ መሆኑ ተገልጿል። የድጋፍ ስምምነቱን የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴና የኖርዌይ የአየር ንብረትና አካባቢ ጥበቃ ሚኒስትር አንድሪያስ ኤሪክሰን ተፈራርመዋል። የድጋፍ ስምምነቱ ኢትዮጵያ በደን ልማትና በአካባቢ ጥበቃ ስራዎች እያከናወነች ያለውን ስራ አጠናክራ እንድትቀጥል የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። የገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ ሁለቱ አገራት በተለያዩ የልማት ስራዎች ላይ በጋራ እየሰሩ መሆኑን አስታውሰው፣ በተለይም በአየር ንብረት ለውጥ ላይ እያከናወነችው ላለው ስራ የኖርዌይ ድጋፍ ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰዋል። በአስር ዓመት የልማት እቅድ ልዩ ትኩረት በመስጠት እየተከናወኑ ከሚገኙ ተግባራት ውስጥ የደን ልማትና የአካባቢ ጥበቃ ስራዎች ተጠቃሽ መሆናቸውን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት ችግኞችን ከመትከል ባለፈ በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን መጠቀምን የሚያበረታታ ፖሊሲ አውጥታ ተግባራዊ እያደረገች መሆኑንም ነው ያነሱት። ደንን በዘላቂነት በማልማት የአየር ንብረት ለውጥን ተጽዕኖ ለመቀነስ የተከናወኑ ስራዎች ውጤታማ ለመሆናቸው ከኖርዌይ የተገኘው ድጋፍ ማሳያ መሆኑን ነው ሚኒስትሩ ያብራሩት። የኖርዌይ የአየር ንብረትና አካባቢ ጥበቃ ሚኒስትር አንድሪያስ ኤሪክሰን በበኩላቸው ኖርዌይ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የምትከተለውን የአረንጓዴ ልማት ፖሊሲ እንደምታደንቅ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባትና የአየር ንብረት አሉታዊ ተጽዕኖን ለመቀነስ ተነሳሽነቱን ወስዳ መስራቷ ሊያስመሰግናት ይገባል ብለዋል። ኖርዌይ ከኢትዮጵያ ጋር በተለያዩ መስኮች በጋራ እየሰራች መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በተለይም ኢትዮጵያ ዘላቂ ልማትን ለማምጣትና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በደን ልማት ላይ እያከናወነችው ያለውን ስራ እንደሚደግፉ አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ በደን ልማት ላይ እያከናወነችው ያለው ስራ አሁን ካለው የበለጠ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትና ለዚህ ደግሞ አገራቸው ድጋፏን አጠናክራ እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል። የገንዘብ ድጋፉ ደንንና የተራቆቱ አካባቢዎችን በዘላቂነት ለማልማትና ለአካባቢ ጥበቃ ስራዎች የሚውል መሆኑ ታውቋል።