አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በጊምቢ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ንጹህ አካባቢን ፈጥሯል
Dec 19, 2025 102
ጊምቢ፤ ታህሳስ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በጊምቢ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት የከተማዋን የቆሻሻ አወጋገድ ክፍተቶች በማረም ንጹህ አካባቢ እንዲኖረን አድርጓል ሲሉ የከተማዋ ነዋሪዎች ተናገሩ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ነዋሪዎች፤ የኮሪደር ልማቱ ከተማዋን ውብ እንድትሆን ከማድረግ ባለፈ የነዋሪዎችን የአኗኗር ዘይቤ እየቀየረ ስለመምጣቱም አክለዋል፡፡ የከተማዋ ነዋሪ የሆኑት አቶ ኢዶሳ ገቢሳ፤ የኮሪደር ልማቱ በአካባቢያቸው ያለውን ሀብት እንዲገነዘቡ ከማድረግ ባለፈ ንጹህና ለኑሮ ምቹ አካባቢ መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡ በኮሪደር ልማት ስራው ልዩ የእግረኛ መንገድ፣ ንጹህ አረንጓዴ ስፍራና ውበትን የሚጨምሩ የመንገድ መብራቶች ዝርጋታ በመከናወኑ ለነዋሪዎች በእግር ለመንቀሳቀስ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡ የኮሪደር ልማቱ ከተማዋ ውበትን እንድትጎናጸፍ እና በአኗኗር ዘይቤያችን ላይ ለውጥ እንዲመጣ አድርጓል ያሉት ደግሞ የከተማዋ ነዋሪ ላሊሳ ቡልቲ ናቸው። በተጨማሪም የልማት ስራው ከዚህ ቀደም ይስተዋሉ የነበሩ የቆሻሻ አወጋገድ ክፍተቶችን በመቅረፍ ንጽህናው የተጠበቀ፣ ተስማሚና ውብ አካባቢ እንዲኖረን አስቸሏል ብለዋል፡፡ ሸህ ሁሴን ጌታሁን የተባሉ ነዋሪ በበኩላቸው፤የኮሪደር ልማቱ የከተማዋን ገጽታ በአጭር ጊዜ ውስጥ በመቀየር ውበትን እንድትጎናጸፍ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡ የጊምቢ ከተማ አስተዳዳር ከንቲባ አቶ ፈዬራ አቦማ፤በከተማዋ የኮሪደር ልማት ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው ቀሪ ስራውን በአጭር ጊዜ ውስጥ አጠናቆ ለአገልግሎት ለማብቃት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። የኮሪደር ልማቱ የእግረኛና የተሽከርካሪ መንገዶች እንዲሁም አረንጓዴ ስፍራዎችን አካቶ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው እስካሁን ወደ ሁለት ኪሎ ሜትር የሚጠጋ የኮሪደር ልማት ስራ መከናወኑን አብራርተዋል። በተለይም የኮሪደር ልማት ለዜጎች የሥራ ዕድል ከመፍጠሩ በላይ ከዩኒቨርሲቲዎች ለተመረቁ ወጣቶች በትምህርት ቆይታቸው የቀሰሙትን በተገቢው በመተገበር ገቢ እንዲያገኙ እያስቻለ ስለመሆኑም ተናግረዋል፡፡ የጊምቢ ከተማን ለኑሮ፣ ለንግድና ለኢንቨስትመንት ምቹ የማድረግ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ከንቲባው አረጋግጠዋል፡፡
በዞኑ ከ251 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የበጋ ወራት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ይከናወናል
Dec 19, 2025 80
ጊምቢ፤ ታህሳስ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምእራብ ወለጋ ዞን ከ251 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የበጋ ወራት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እንደሚከናወን ተገለጸ፡፡ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች ከ33 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ማልማት መቻሉን ከግብርና ሚኒስቴር የተገኘ መረጃ ያመለክታል። ዘንድሮም ይኸው ተግባር በተለያዩ ክልሎች በተጠናከረ ሁኔታ እየተከናወነ ሲሆን በኦሮሚያ ክልልም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው አርሶ አደሮችን ባሳተፈ መልኩ እየተካሄደ ነው። በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች ከ3 ሚሊዮን ሄክታር በላይ የሚሆን መሬትን ወደ ልማት እንዲገባ በማድረግ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት የማጎልበት ስራ ተሰርቷል። አሁን ላይም በክልሉ በሚገኙ ዞኖች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው በተጠናከረ ሁኔታ እየተከናወነ ሲሆን ከነዚሁ ዞኖች አንዱ በሆነው በምዕራብ ወለጋ ዞን በተያዘው የበጋ ወራት ከ251 ሺህ ሄክታር በላይ በሆነ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እንደሚከናወን የዞኑ ግብርና ፅህፈት ቤት አስታውቋል። በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ፍቅሩ ብርሃኑ እንደተናገሩት፤ በዞኑ በለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የአፈር መሽርሸርን በማስቀረት፣ የከርስ ምድርና ገጸ ምድር ውሀ ሀብት በመጨምርና የግብርና ምርታማነት በማሳደግ በኩል ተጨባጭ ለውጥ አምጥተዋል፡፡ በዘንድሮ በጋ ወራትም በ251 ሺህ 471 ሄክታር መሬት በላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች እንደሚከናወኑ ገልጸው በስራውም ከ400 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች እንደሚሳተፉ አክለዋል፡፡ አርሶ አደሮቹ በንቃት እንዲሳተፉ በማድረግ የእርከን ስራዎች፣ የውሃ መቀልበሻ ቦዮችና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች እንደሚከናወኑ ጠቁመዋል፡፡ ስራውን ለማሳካትም ካለፉት ዓመታት የተገኙ ልምዶችን በመቀመር የህብረተሰብ ንቅናቄ ስራ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አክለዋል። ባለፉት ጊዜያት በተከናወኑት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ከልማት ወጪ የነበሩ አካባቢዎች ዳግም ወደ ልማት መግባታቸውን ጠቁመዋል፡፡ የአካባቢዎቹ መልማትም ህብረተሰቡ አካባቢውን እየጠበቀ ከልማቱ ጋር የተሳሰሩ እንደ የንብ ማነብ፣ የከብቶች መኖ ልማት እና ሌሎች የልማት ተግባራትን እንዲያከናውን ዕድል እንደተፈጠረለት ገልጸዋል።
በሀገር አቀፍ ደረጃ የተከናወኑ የልማት ስራዎች ፅዱ ኢትዮጵያን ለመፍጠር የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት እያስቻሉ ነው
Dec 18, 2025 93
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 9/2018 (ኢዜአ)፡-በሀገር አቀፍ ደረጃ የተከናወኑ የአካባቢ ጥበቃና የልማት ስራዎች ፅዱ ኢትዮጵያን ለመፍጠር የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት እያስቻሉ መሆኑ ተገለፀ። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የአካባቢ ጥበቃን በተመለከተ በወጡ ሕጎች፣ ደንቦች፣ ማዕቀፎችና አሰራሮች ላይ ከሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ለተውጣጡ ባለድርሻ አካላት የአቅም ግንባታ ስልጠና መስጠት ጀምሯል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ለሊሴ ነሜ በወቅቱ እንደገለጹት፤ መንግስት ባለፉት ጥቂት ዓመታት በሀገር አቀፍ ደረጃ ተግባራዊ ያደረጋቸው የልማት ስራዎች ውጤታማ ናቸው። በተለይም የኮሪደር ልማትን ጨምሮ የተከናወኑ ተግባራት ጽዱ ኢትዮጵያን ለመፍጠር የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት ትልቅ ሚና እየተጫወቱ እንደሚገኙ ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የአካባቢ ጥበቃና ልማት ስራዎችን በተጠናከረ መልኩ ለማስቀጠል የሚያስችሉ የለውጥ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑንም አንስተዋል። የአካባቢ ጥበቃ ስራ የመንግስት ወይም የአንድ ተቋም ኃላፊነት አለመሆኑን ያመለከቱት ዋና ዳይሬክተሯ፤ ህብረተሰቡንና የተለያዩ ተቋማትን በማስተባበር ቀጣይነት ያለው የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ምርምር ማዕከል ኃላፊ ፕሮፌሰር በላይ ሰማኒ በበኩላቸው፤ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎችን ከዘላቂ የልማት ግቦች በማቀናጀት ትኩረት ሊሰጣቸው እንደሚገባ ገልጸዋል። ስለሆነም የአካባቢ ጥበቃ ፖሊሲዎችንና አዋጆችን በአግባቡ ተግባራዊ በማድረግ ዘላቂ የልማት ዕቅዶችን ለማሳካት በትኩረት መሥራት እንደሚገባ አሳስበዋል። የተመድ የልማት ፕሮግራም (UNDP) የኢትዮጵያ ተወካይ ሳሙኤል ባይድ ዶ በበኩላቸው፤ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር፣ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ እንዲሁም የካርበን ልቀትን ለመቀነስ የተከናወኑ ሥራዎች ውጤታማ መሆናቸውን በተጨባጭ መመልከታቸውን ጠቅሰዋል። ይህ ስልጠናም በኢትዮጵያ የተጀመሩ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎችን ከሀገራዊ የልማት ዕቅዶች ጋር አጣጥሞ ለማስኬድ የሚያስችል አቅም ይፈጥራል ብለዋል።
በደረቅ ቆሻሻ መልሶ መጠቀም ላይ የተሰማሩ ማህበራት ለከተማዋ ጽዳት መጠበቅ ከፍተኛ ድርሻ አላቸው
Dec 18, 2025 113
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 9/2018 (ኢዜአ)፡-በአዲስ አበባ በደረቅ ቆሻሻ መልሶ መጠቀም ላይ የተሰማሩ ማህበራት ለከተማዋ ጽዳት መጠበቅ የድርሻቸውን በመወጣት ላይ እንደሚገኙ ተገለጸ። የምግብ ማሸግያዎች፣ የዕቃ መጠቅለያዎች፣ ቁርጥራጭ ወረቀቶች፣ የውሃ ማሸጊያ ፕላስቲኮች፣ የኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎችና በአጠቃላይ አገልግሎት ሰጥተው ያበቁ አልባሳትን ጨምሮ ሌሎች ቁሳቁሶች በደረቅ ቆሻሻ ውስጥ ይመደባሉ፡፡ እነኚህ ቁሳቁሶች በአግባቡ ካልተወገዱ አካባቢን በመበከል በሰውም ሆነ በእንስሳት ጤና ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድራሉ፡፡ በአግባቡ ከተከማቹና ከተያዙ ደግሞ መልሰው ጥቅም ላይ ሊውሉ ከመቻላቸውም በላይ ሀብት ሆነው ለሌሎች ወገኖች የስራ ዕድል መፍጠር ያስችላሉ፡፡ በመዲናዋ ኢዜአ ያነጋገራቸውና በዘርፉ የተሰማሩ ማህበራት የፕላስቲክ ውጤቶችና የኤሌክትሮኒክስ ምርቶችን መልሶ በመጠቀም የተሻለ ገቢ ከማግኘት ባለፈ ጽዱና ንጹህ አካባቢ ለመፍጠር የድርሻችንን በመወጣት ላይ እንገኛለን ብለዋል፡፡ የኢኬቲ ንግድና ኢንቨስትመንት ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ድርጅት ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ ዳንኤል መኮንን፤ የፕላስቲክ ውጤቶች ቶሎ ስለማይበሰብሱ ለአካባቢ ብክለት ዋነኛ መንስኤ ናቸው ብለዋል፡፡ ድርጅታቸው የፕላስቲክ ውጤቶችን መልሶ በመጠቀም ለቤት ውስጥ መገልገያና ለተለያዩ ዕቃዎች ማሸጊያ እንዲውሉ በማድረግ ላይ መሆኑን ተናግረዋል ። በዚህም የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ንጹህ አካባቢ ከመፍጠር ባለፈ አራት መቶ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠሩን ገልጸዋል፡፡ የሄፊሊ ኤሌክትሮኒክስ ዕቃዎች መልሶ መጠቀም ድርጅት ማናጀር አቶ ቴዎድሮስ ካሳው፤ የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች በአግባቡ ካልተወገዱ ለሰውና ለእንስሳት ጤና ስጋት መሆናቸውን ተናግረዋል። ድርጅታቸው ከተበላሹ የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች ብረት፣ አልሙኒዬምና መዳብ በማውጣት መልሰው አገልግሎት እንዲሰጡ በማድረግ ላይ ይገኛል ብለዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ የፅዳት አስተዳደር ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ገዛኸኝ ዴሲሳ ፤ከተማዋን ስማርት ሲቲ ለማድረግ የሚያስችሉ መሰረተ ልማቶች፣ መዝናኛ ፓርኮችና አረንጓዴ አካባቢዎች በስፋት መገንባታቸውን ተናግረዋል፡፡ ኤጀንሲው የመሰረተ ልማቶቹን ዘላቂነት ለማረጋገጥ በደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ላይ አበክሮ እየሰራ እንደሚገኝም አስታውቀዋል፡፡ በዚህም በደረቅ ቆሻሻ መልሶ መጠቀም ላይ የተሰማሩ ማህበራት ለከተማዋ ጽዳት መጠበቅ ከፍተኛ ድርሻ መውሰዳቸውን ተናግረዋል፡፡ በ2017 በጀት ዓመት በመልሶ መጠቀም የተሰማሩ ማህበራት ከ1 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ጠቅሰው፤ በተያዘው በጀት ዓመት የመጀመሪያው ሩብ ዓመትም 515 ሚሊየን ብር ገቢ እንዳገኙ ተናግረዋል፡፡ ኤጀንሲው በዘርፉ ለተሰማሩ ኢንዱስትሪዎች የገበያ ትስስር በመፍጠር ላይ እንደሚገኝ አስታውቀዋል፡፡
በጎርጎቻ ተራራ ላይ በተሰራ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የተፈጥሮ ሀብቱን መታደግ ተችሏል
Dec 18, 2025 130
ጂንካ፤ታህሳስ 9/2018 (ኢዜአ)፡- በአሪ ዞን ባለፉት ሶስት ዓመታት ጎርጎቻ ተራራ ላይ በተሰራ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የተፈጥሮ ሀብቱን ከመጥፋት መታደግ እንደቻሉ የባካዳውላ አሪ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለፁ። የጎርጎቻ ተራራ በጂንካ ከተማ እና በባካዳውላ አሪ ወረዳ አዋሳኝ የሚገኝ ተራራ ነው። ተራራው ከዚህ ቀደም ትኩረት ባለማግኘቱ ምክንያት የመራቆት አደጋ አጋጥሞት እንደነበር የአከባቢው አርሶ አደር ወንድይፍራው ፈለቀ ያስታውሳሉ። በተራራው ላይ ያለው ደን በመመናመኑ በአከባቢው በተደጋጋሚ የጎርፍ አደጋ ይከሰት እንደነበር ጠቁመው አልፎ አልፎ በሰውና በእንስሳት ላይ ጉዳት እንደሚያጋጥም ተናግረዋል። የእርሻ ማሳቸውም በጎርፍ በመታጠቡ ለምነቱን ማጣቱን እና ምርት መስጠት አለመቻሉን ጠቁመው ባለፉት ሶስት አመታት በተራራው ላይ በተጀመረው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ተራራውንና የተፈጥሮ ሀብቱን መታደግ መቻሉን ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደም ለተለያዩ አገልግሎት ሲጠቀሙበት የነበረ ምንጭ የመድረቅ አደጋ አጋጥሞት እንደነበረ ያስታወሱት አርሶ አደሩ ተራራው መልማት ከጀመረ ወዲህ የውሃ ምንጮች መጠናቸው እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል። ሌላው አስተያየት ሰጪ አርሶ አደር ካሳ ሰኒ በበኩላቸው የጎርጎቻ ተራራ ለመድሃኒትነት የሚውሉ በርካታ ዕፅዋት እንዳለው ጠቁመው ከደኑ የሚወጣው ንፁህ አየርም የመንፈስ እርካታን የሚሰጥ ነው ብለዋል። "ባለማወቅ ከዚህ ቀደም የተፈጥሮ ሀብቱን ያለ አግባብ ስንጨፈጭፍ ነበር" ያሉት አርሶ አደሩ በአሁኑ ሰዓት ተራራው የቀድሞ ግርማ ሞጎሱን እየተላበሰ መምጣቱንና ተራራው በመልማቱ የጎርፍ አደጋን መከላከል እንዳስቻለ ተናግረዋል። በአሪ ዞን ግብርና መመምሪያ የተፋሰስ ልማት ባለሙያ መንግሥቱ አስፋው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የተራቆቱ አከባቢዎች እንዲያገግሙ በማድረግ ተስማሚ ስነ-ምህዳር እንዲፈጠር አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። በዞኑ የጎርጎቻ ተራራን ጨምሮ በየአካባቢው ያለውን ተፋሰስ ለማልማት ወደ ተግባር መገባቱንና በዚህም ተጨባጭ ለውጦች መምጣታቸውን ገልጸዋል። ባለፈው አመት በዞኑ በ21 ሺህ 986 ሄክታር መሬት 105 ንዑስ ተፋሰሶች መልማታቸውን ጠቁመው 212 ሺህ የሚሆኑ የማህበረሰብ ክፍሎች በልማቱ መሳተፋቸውንም ጠቁመዋል። በዘንድሮ አመትም ከታህሳስ መጨረሻ ጀምሮ የተፋሰስ ልማት ንቅናቄ ለማድረግ የሚያስችሉ የቦታ መረጣና አስፈላጊ ቅድመ ዝግጅቶች መከናወናቸውን ገልጸዋል። በዘንድሮ የተፋሰስ ንቅናቄም በዞኑ 24 ሺህ 97 ሄክታር መሬት ላይ 106 ንዑስ ተፋሰሶች የሚለሙ ሲሆን 131 ሺህ የማህበረሰብ ክፍሎችን ለማሳተፍ ዕቅድ መያዙን ተናግረዋል።
የኮንሶዎች እርከን ሥራ ለተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ጉልህ አስተዋጾ እያበረከተ ነው
Dec 18, 2025 97
ካራት ፤ ታህሳስ 9/2018(ኢዜአ)፡-በዓለም አቀፍ ቅርስነት የተመዘገበው የኮንሶዎች እርከን ሥራ ለተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ጉልህ አስተዋጾ ያበረከተ ሀገር በቀል እውቀት መሆኑ ተገለጸ፡፡ የኮንሶ መልክአ ምድር በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በ2003 ዓ.ም በዓለም ቅርስነት መመዝገቡ የሚታወስ ነው። መልክአ ምድሩ በ23 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ያረፈና በውስጡ በርካታ ቅርሶችን የያዘ ሲሆን የእርሻ እርከኖች፣ ጥብቅ ደኖች፣ ኩሬዎችና መንደሮች ይገኙበታል፡፡ የኮንሶ ዞን ግብርና መምሪያ ምክትልና የእርሻ ዘርፍ ሃላፊ ወይዘሮ ገንዘቤ ኮራ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በዓለም አቀፍ ቅርስነት የተመዘገበው የኮንሶዎች እርከን ሥራ ለተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ጉልህ ፋይዳ እያበረከተ ያለ ሀገር በቀል አውቀት ነው። ባህላዊ የእርከን ሥራው የኮንሶ ማህበረሰብ የታታሪነት ምልክት መሆኑን ገልጸው፣ ማህበረሰቡ አስቸጋሪ መልክአ ምድርን ጭምር በማልማት ውጤታማ መሆን እንደሚቻል ያሳየበት እንደሆነም ተናግረዋል። የእርከን ሥራው ኮንሶዎች ትውልድን የተሻገረ ቅርስና ተፈጥሮን ለመጠበቅ የዘየዱት ሃገር በቀል እውቀት ሲሆን የአፈር መሸርሸርን ከመከላከል ባለፈ የዝናብ ውሃን ወደመሬት በማስረግ ለምርትና ምርታማነት ማደግ ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። እንደ ሃላፊዋ ገለጻ በአካባቢው ከአዝርዕት ሰብሎች በቆሎ፣ ማሽላ፣ ጤፍ፣ ቦሎቄ እና ዳጉሳን እንዲሁም የጓሮ አትክልቶች በተለይ በመኸርና በበልግ ወቅቶች በስፋት ይመረታሉ። በጥምር ግብርና የሚተዳደሩት ኮንሶዎች ተፈጥሮን ጠብቀው በስፋት ለሚያከናውኑት የእንስሳት እርባታ ስራም ከሰብል ተረፈ ምርት በተጨማሪ የመኖ ዛፎችን እንደሚያለሙም ተናግረዋል። የኮንሶ ዞን ህዝብ የባህል አባት ካላ ገዛኸኝ ወልዳዊት በበኩላቸው የኮንሶዎች ባህላዊ የእርከን ሥራ የህዝቡ የአኗኗር ዘይቤ መገለጫና የሀገር በቀል ዕውቀት ውጤት ነው ብለዋል። የጥንት ኮንሶዎች የስልጣኔ ምልክት የሆነው የእርከን ሥራ ከአካባቢው የአየር ጸባይ ጋር እንዴት ተስማምቶ መኖር እንደሚቻል ትውልድ የተማረበት መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ የእርከን ሥራው አፈር እንዳይሸረሸር እንዲሁም ለምነትና እርጥበቱ ተጠብቆ እንዲቆይ በማድረግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የማይተካ ሚና እንዳለውም ገልጸዋል። የኮንሶ ማህበረሰብ ባህላዊ የእርከን ሥራ ከመኖሪያ መንደር ጀምሮ እስከ አርሻ ማሳ በጥንቃቄ የሚሠራ የህልውና መገለጫ ነው ያሉት ደግሞ አቶ ሮባ ለሚታ የተባሉ የአካባቢው ነዋሪ ናቸው። ያለን ትልቁ ሀብት መሬት ነው ያሉት አስተያየት ሰጪው እርከን ሥራም መገለጫችን ነው ብለዋል። የተፈጥሮ ሀብትን በአግባቡ መጠበቅ ካልተቻለ ትውልድ የማስቀጠል ጉዳይ አደጋ እንደሚገጥመው ገልጸው፣ "ከአባቶች የተረከብነውን ቅርስ ጠብቀን ለልጆቻችን እናስተላልፋለን" ብለዋል። የኮንሶ የመሬት አቀማመጥና የአየር ጸባይ ምቹ ባይሆንም አባቶች እርከን በመስራትና በባህላዊ ኩሬ ውሃ በማቆር ተፈጥሮን ተቋቁሞ መኖር የሚቻልበትን ዘዴ እንዳስተማራቸው ገልጸዋል፡፡ የኮንሶ ማህበረሰብ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃን ያለውን ጠቀሜታ ቀድሞ መገንዘቡን የገለጹት አቶ ሮባ፣ በዚህም የተፋሰስ ሥራ በማከናወን ለምርታማነት መረጋገጥ የበኩሉን እየተወጣ ይገኛል ብለዋል። የኮንሶዎች ሀገር በቀል ዕውቀት ውጤት የሆነው የእርከን ሥራ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ አካባቢዎችም በስፋት እየታየ ነው።
በአማራ ክልል የበጋ ወራት የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው
Dec 17, 2025 168
ባህር ዳር ፤ ታህሳስ 8/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የበጋ ወራት የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ ግብርና ቢሮ የተፈጥሮ ሃብት ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት፤ የበጋ ወራት የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በመከናወን ላይ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች በ9 ሺህ 206 ተፋሰሶች ላይ በ456 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የበጋ ወራት የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ቀጥሏል ብለዋል። የበጋ ወራት የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራው እስከ መጪው መጋቢት ወር የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል። በዚህ የልማት ስራ ላይ ከ4 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ አርሶ አደሮች የሚሳተፉ መሆኑን አንስተው የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ትብብርና ተሳትፎም መጠናከር አለበት ብለዋል። በበጋው የተቀናጀ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ የማሳና የጋራ ላይ እርከን፣ የውሃ ማፋሰሻና መቀልበሻ ቦዮች እንዲሁም ከ6 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ የውሃ ማስረጊያ ስትራክቸሮች የሚከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። በክልሉ የልማት ስራው ከሚከናወንባቸው አካባቢዎች መካከል የደቡብ ጎንደር ዞን የፋርጣ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አራጋው ወንዴ እና በምዕራብ ጎንደር ዞን ገንዳ ውኃ ዙሪያ ነዋሪ አርሶ አደር የሱፍ ይመር፤ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ መሰረታዊ ጉዳይ አድርገን እየሰራን ነው ብለዋል። በዚህ የልማት ስራ የእርሻ መሬትና የአፈር ለምነት እንዲሻሻልና ምርታማነት እንዲጨምር ከማድረግ ባለፈ በተፋሰሶቹ የእንስሳት መኖ ማግኘት እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ ባለፈው ዓመት በ8 ሺህ 400 ተፋሰሶች ላይ የበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃ ስራ መከናወኑ ታውቋል።
በክልሉ ለዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ሥራ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Dec 17, 2025 93
ቦንጋ ፤ ታህሳስ 8/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ዘንድሮ ከ272 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ለሚከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። በክልሉ የመሬትና የውሃ ሀብትን መጠበቅ፣ ማልማትና በላቀ ደረጃ አቀናጅቶ ጥቅም ላይ ለማዋል ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ውብሸት ዘነበ ለኢዜአ ተናግረዋል፡፡ በየዓመቱ የሚከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈር ለምነትን ለመመለስና የውሃ ሀብትን ለማበልፀግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች ምርትና ምርታማነት መጨመሩን ያነሱት አቶ ውብሸት፣ በተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ የለሙ አካባቢዎች ለበርካታ ወጣቶች የሥራ ዕድል እንደፈጠሩም ገልጸዋል። ዘንድሮም ልማቱን አጠናክሮ ለማስቀጠል በከፍተኛ የህዝብ ንቅናቄ በልዩ ትኩረት ይሰራል ብለዋል። በክልሉ ከጥር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ 30 ቀናት በሚከናወነው የአፈርና ውሃ ልማትና ጥበቃ ሥራ ከ1 ሚሊዮን 305 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለማሳተፍ መታቀዱንም ጠቁመዋል፡ የዘንድሮ የበጋ ወቅት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ በ1ሺህ 210 ተፋሰሶች በሚገኝ 272 ሺህ 250 ሄክታር መሬት ላይ እንደሚከናወንም አቶ ውብሸት አስታውቀዋል። ለሥራው ውጤታማነት የአሰልጣኞች ስልጠና መስጠት፣ ለልማቱ የሚያስፈልጉ መሳሪያዎችን ማሟላት እንዲሁም የልማቱ ተሳታፊ የህብረተሰብ ክፍሎችን መለየትና ሌሎች የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በዚህ ዓመት በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና በተፋሰስ ልማት 4 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሔክታር መሬት ይለማል-የግብርና ሚኒስቴር
Dec 14, 2025 243
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 5/2018(ኢዜአ)፦ በዚህ ዓመት በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና በተፋሰስ ልማት 4 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሔክታር መሬት እንደሚለማ የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ፡፡ በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማትና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈጻሚ ፋኖሴ መኮንን፤ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ እና የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ በማህበረሰቡ ዘንድ ባህል እየሆነ መጥቷል ብለዋል፡፡ በየዓመቱ በሀገሪቱ ሁሉም አካባቢዎች በህብረተሰብ ንቅናቄ የአፈር እና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ የተራቆቱ መሬቶች እንዲያገግሙ፤ የአፈር መሸርሸርን በመከላከል ለምነት እንዲጨምርና ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ እያደረገ ነው ብለዋል። ከዚህ ባለፈም ወጣቶች ተደራጅተው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውን አትክልቶችንና ፍራፍሬዎችን እንዲያመርቱ በማስቻል ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያሳደገ መሆኑን ተናግረዋል። የዘንድሮው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የተፋሰስ ልማት ንቅናቄ በሀገር አቀፍ ደረጃ ጥር ወር ላይ በይፋ እንደሚጀመር ጠቅሰው፥ ለዚህም የዝግጅት ስራው በመጠናቀቅ ላይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህ ዓመት በ21 ሺህ ተፋሰሶች በሚከናወነው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ሥራ 4 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሔክታር መሬት እንደሚለማ አስረድተዋል፡፡ የተፈጥሮ ሃብት ስራ የተፈጥሮ ሚዛንን በመጠበቅ ለአየር ንብረት ለውጥ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያለው በመሆኑ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በንቅናቄው ወጥቶ መስራት እንዳለበትም ጥሪ አቅርበዋል። በሚከናወነው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ በድርቅ እና በአካባቢ መራቆት የተጎዱ አካባቢዎች መልሰው እንዲያገግሙ ይደረጋል ብለዋል። በየዓመቱ በህዝብ ንቅናቄ በሚከናወነው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ በአማካይ ከ14 ሚሊዮን በላይ ሰዎች እንደሚሳተፉ ተናግረዋል፡፡ በዚህም ህብረተሰቡ በአማካይ በየዓመቱ ከ18 ቢሊዮን ብር በላይ የሚገመት ጊዜ፣ ጉልበትና ሀብት አስተዋጽኦ የሚያደርግበት መሆኑን ነው የገለጹት፡፡
ኮፕ-32 ጉባኤን የበለጠ ስኬታማ ለማድረግ ባለሃብቶች ሚናቸውን መወጣት አለባቸው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Dec 12, 2025 293
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ የምታስተናግደው 32ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት (ኮፕ-32) ጉባኤን የበለጠ ስኬታማ ለማድረግ ባለሃብቶች ሚናቸውን መወጣት እንዳለባቸው የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ የምታስተናግደውን የመንግሥታቱ ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ /ኮፕ-32/ በተመለከተ የባለድርሻ አካላት የውይይት መድረክ በአራዳ ፓርክ ተካሂዷል። በመርሀ ግብሩ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊ እና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሀይ ጳውሎስ፣ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን፣ የመዲናዋ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የተለያዩ ባለብቶች እንዲሁም አልሚዎች ተገኝተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤን እንድታዘጋጅ የተመረጠችው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሳል የዲፕሎማሲ አመራር የተገኘ ስኬት ነው። ይህም ትልቅ የዲፕሎማሲ ድል መሆኑን ነው ከንቲባ አዳነች አቤቤ የተናገሩት። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብር፣ በከተሞች ልማትና ውበት የተመዘገቡ ውጤቶች ዓለም አቀፉን ጉባኤ እንድታስተናግድ ተመራጭ አድርጓታል ብለዋል። ኢትዮጵያ ብሎም አዲስ አበባ የዓለም የስበት ማዕከል መሆናቸውን በመጥቀስ፣ መዲናዋ ባለፈው ዓመት በርካታ ዓለም አቀፍ፣ አሕጉራዊ እና ሀገራዊ ሁነቶችን ማስተናገድ መቻሏን ገልጸዋል። ኮፕ-32 የዓለማችን ትልቁ የትኩረት ማዕከል መሆኑንም ነው የተናገሩት። ጉባኤው ለኢትዮጵያውያን ብዙ ዕድል ይዞ ይመጣል ያሉት ከንቲባዋ፤ ለዚህ ደግሞ መንግሥት የመሪነት ሚናውን እንዲወጣ ባለድርሻ አካላት በትብብር መስራት እንዳለባቸው ገልጸዋል። ጉባኤው ኢትዮጵያ በቀጣይ ሌሎች ዓለም አቀፍ ሁነቶችን የማዘጋጀት ዕድል እንድታገኝ፣ የኢትዮጵያን ነባራዊ ሁኔታ ለማሳየትና የስራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ ነው ብለዋል። በመሆኑም ባለሀብቶች አልሚዎችና አጠቃላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከመንግሥት ጋር በመተባበር ጉባኤውን በስኬት ለማካሄድ ከወዲሁ ዝግጅት ማድረግ እንዳለባቸው አስረድተዋል። ጉባኤውን በብቃት በማስተናገድ ለኢትዮጵያ ለውጥ መሰረት መጣል አለብን ያሉት ከንቲባዋ፤ ዛሬ የስራ ክፍፍል በማድረግና ዝግጅት በመጀመር ግባችንን ማሳካት አለብን ብለዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሀይ ጳውሎስ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ሁነቶችን የማስተናገድ አቅሟ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ዓለም አቀፋዊ፣ አህጉራዊና ሀገራዊ ኮንፍረንሶችን በብቃት ማስተናገድ የሚያስችል አቅም መፈጠሩን ገልጸው፤ ውጤቱም በጋራ ትብብር የተመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል። እንደ ሀገር ያስመዘገብናቸው ስኬቶች ለቀጣይ ስራዎቻችን መስፈንጠሪያ እንደሚሆኑ በመጥቀስ፤ ኮፕ-32 እንዲሁ የተገኘ አይደለም ብለዋል። ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤ አዘጋጅነትን ለማግኘት ዓለም አቀፋዊ ውድድር ማድረግ ነበረባት ያሉት ኃላፊዋ፤ በአረንጓዴ ዐሻራ እና በሌሎችም አረንጓዴ ልማት ስራዎች በተገኙ ውጤቶች መመረጧን በመግለጽ። ኢትዮጵያ በተያዘው በጀት ዓመት አምስት ወራት ከ105 በላይ ሁነቶችን ማዘጋጀቷን ገልጸው፤ እነዚህ ስኬቶች የኮፕ 32 ጉባኤ ዝግጅትን በድል እንደምንወጣ የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉ ባለሃብቶችና አልሚዎች በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ኮፕ-32 ለማስተናገድ መመረጧ ትልቅ ዕድል ይዞ ይመጣል ብለዋል፡፡ በጉባኤው የሚሳተፉ አካላት የውጭ ምንዛሪ ይዘው እንደሚመጡ በማንሳት፤ በቆይታቸው የአገልግሎት ዘርፉን ገቢ ለማሳደግ ገንቢ ሚና እንደሚኖራቸው ገልጸዋል፡፡ ኮፕ-32 የኢትዮጵያ የዲፕሎማሲያ ስኬት ማሳያ እንዲሁም ለገጽታ ግንባታ የጎላ አበርክቶ እንዳለውም ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያ ጉባኤውን በስኬት ማስተናገድ እንድትችል ከመንግስት ጎን በመሆን አስፈላጊውን ትብብር እንደሚያደርጉ አረጋግጠዋል፡፡ በብራዚል ቤለም በተካሄደው 30ኛ ጉባኤ ላይ ከሁለት ዓመታት በኋላ የሚካሄደውን 32ኛ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤ (COP-32) ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ መመረጧ ይታወቃል።
ኢትዮጵያ ኮፕ-32 ጉባኤን እንድታዘጋጅ መመረጧ ዲፕሎማሲያዊ ስኬት ነው
Dec 12, 2025 222
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 32ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት(ኮፕ-32) ጉባኤን እንድታዘጋጅ መመረጥ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሳል የዲፕሎማሲ አመራር የተገኘ ስኬት መሆኑን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ኢትዮጵያ የምታስተናግደውን የመንግሥታቱ ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ /ኮፕ-32/ በተመለከተ የባለድርሻ አካላት የውይይት መድረክ በአራዳ ፓርክ ተካሂዷል። በመርሀ ግብሩ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊ እና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሀይ ጳውሎስ፣ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን፣ የመዲናዋ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የተለያዩ ባለሃብቶች እንዲሁም አልሚዎች ተገኝተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤን እንድታዘጋጅ የተመረጠችው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሳል የዲፕሎማሲ አመራር የተገኘ ስኬት ነው። ይህም ትልቅ የዲፕሎማሲ ድል መሆኑን ነው ከንቲባ አዳነች አቤቤ የተናገሩት። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብር፣ በከተሞች ልማትና ውበት የተመዘገቡ ውጤቶች ዓለም አቀፉን ጉባኤ እንድታስተናግድ ተመራጭ አድርጓታል ብለዋል። ኢትዮጵያ ብሎም አዲስ አበባ የዓለም የስበት ማዕከል መሆናቸውን በመጥቀስ፣ መዲናዋ ባለፈው ዓመት በርካታ ዓለም አቀፍ፣ አሕጉራዊ እና ሀገራዊ ሁነቶችን ማስተናገድ መቻሏን ገልጸዋል። ኮፕ-32 የዓለማችን ትልቁ የትኩረት ማዕከል መሆኑንም ነው የተናገሩት። ጉባኤው ለኢትዮጵያውያን ብዙ ዕድል ይዞ ይመጣል ያሉት ከንቲባዋ፤ ለዚህ ደግሞ መንግሥት የመሪነት ሚናውን እንዲወጣ ባለድርሻ አካላት በትብብር መስራት እንዳለባቸው ገልጸዋል። ጉባኤው ኢትዮጵያ በቀጣይ ሌሎች ዓለም አቀፍ ሁነቶችን የማዘጋጀት ዕድል እንድታገኝ፣ የኢትዮጵያን ነባራዊ ሁኔታ ለማሳየትና የስራ ዕድል ለመፍጠር ወሳኝ ነው ብለዋል። በመሆኑም ባለሀብቶች አልሚዎችና አጠቃላይ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከመንግሥት ጋር በመተባበር ጉባኤውን በስኬት ለማካሄድ ከወዲሁ ዝግጅት ማድረግ እንዳለባቸው አስረድተዋል። ጉባኤውን በብቃት በማስተናገድ ለኢትዮጵያ ለውጥ መሰረት መጣል አለብን ያሉት ከንቲባዋ፤ ዛሬ የስራ ክፍፍል በማድረግና ዝግጅት በመጀመር ግባችንን ማሳካት አለብን ብለዋል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሀይ ጳውሎስ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ሁነቶችን የማስተናገድ አቅሟ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ዓለም አቀፋዊ፣ አህጉራዊና ሀገራዊ ኮንፍረንሶችን በብቃት ማስተናገድ የሚያስችል አቅም መፈጠሩን ገልጸው፤ ውጤቱም በጋራ ትብብር የተመዘገበ መሆኑን ተናግረዋል። እንደ ሀገር ያስመዘገብናቸው ስኬቶች ለቀጣይ ስራዎቻችን መስፈንጠሪያ እንደሚሆኑ በመጥቀስ፤ ኮፕ-32 እንዲሁ የተገኘ አይደለም ብለዋል። ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤ አዘጋጅነትን ለማግኘት ዓለም አቀፋዊ ውድድር ማድረግ ነበረባት ያሉት ኃላፊዋ፤ በአረንጓዴ ዐሻራ እና በሌሎችም አረንጓዴ ልማት ስራዎች በተገኙ ውጤቶች መመረጧን በመግለጽ። ኢትዮጵያ በተያዘው በጀት ዓመት አምስት ወራት ከ105 በላይ ሁነቶችን ማዘጋጀቷን ገልጸው፤ እነዚህ ስኬቶች የኮፕ 32 ጉባኤ ዝግጅትን በድል እንደምንወጣ የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል። በብራዚል ቤለም በተካሄደው 30ኛው ጉባኤ ላይ ከሁለት ዓመታት በኋላ የሚካሄደውን 32ኛ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤ(COP-32) ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ መመረጧ ይታወቃል።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የሌሊቱና የማለዳው ቅዝቃዜ አንጻራዊ ጥንካሬ ይኖረዋል -የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት
Dec 12, 2025 196
አዲስ አበባ ታህሳስ 3/2018 (ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አስር ቀናት በሰሜን፣ ምስራቅ፣ መካከለኛው እና ደቡብ ደጋማ የአገሪቱ ክፍሎች የሌሌቱና የማለዳው ቅዝቃዜ አንጻራዊ ጥንካሬ እንደሚኖረው የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ለኢዜአ በላከው መግለጫ የበጋው ደረቅ፣ ፀሐያማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ በአብዛኛዎቹ የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ እንደሚስተዋል አስታውቋል። በሚቀጥሉት አስር ቀናት ከሳይቤሪያ ከፍተኛ የአየር ግፊት በመነሳት ወደ አገራችን የሚነፍሰው ደረቅ እና ቀዝቃዛ የአየር ሁኔታ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ ብሏል። በአንዳንድ አካባቢዎች ቅዝቃዜው ከአምስት ዲግሪ ሴልሺየሽ በታች እንደሚሆን የትንበያ መረጃዎች እንደሚያሳዩ አስታውቋል። በዚህም በሰሜን ፣ሰሜን ምስራቅ፣ ምስራቅ፣ መካከለኛው እና ደቡብ ደጋማ የአገሪቱ ክፍሎች የሌሊቱና የማለዳው ቅዝቃዜ አንጻራዊ ጥንካሬ እንደሚኖረው ገልጿል። አልፎ አልፎ በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ ውርጭ የማስከተል ጥንካሬ እንደሚኖረውም ጠቁሟል። በጋ ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት የደቡብና ደቡብ ምስራቅ የአገሪቱ አካባቢዎች የሚገኙ ጥቂት ቦታዎች ቀላል መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ ብሏል። በተጨማሪም በሰሜን ምዕራብ፣ ምዕራብ እና ደቡብ ምዕራብ የአገሪቱ ክፍሎች አልፎ አልፎ አነስተኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖር የትንበያ መረጃዎች እንደሚያመላክቱ ገልጿል። በዚሁ ወቅት አብዛኛው ተፋሰሶች ደረቅ የአየር ሁኔታ እንደሚስተዋል አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ ብሏል።
በክልሉ በመጪው ክረምት ለሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ችግኝ እየተዘጋጀ ነው
Dec 12, 2025 157
ባህርዳር ፤ ታህሳስ 3/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በመጪው ክረምት ለሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ እየተዘጋጀ መሆኑ ተመላከተ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ እንደሀገር በተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የተራቁቱ መሬትን መልሶ በደን በመሸፈን እና የከርሰ ምድርና ገጸ ምድር ውሀ ሀብትን በማሳደግ ተጨባጭ ውጤት እያተመዘገበ ይገኛል። ባለፉት አመታት ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ በትኩረት በተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የክልሉን የደን ሽፋን ወደ 18 በመቶ ማሳደግ እንደተቻለም የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ መረጃ ያመለክታል። በቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በተለያየ ምክንያት የተራቆተውን መሬት በደን መልሶ ለማልበስና የአየር ንብረት ሚዛኑን ለማስተካከል የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ከፍተኛ ድርሻ አበርክቷል። ተግባሩን ለማስቀጠልም በመጪው ክረምት ለሚተከሉ ችግኞች በመንግስት፣ በተቋማት፣ በማህበራትና በግል ተቋማት እንዲሁም ከ75 ሺህ በሚበልጡ የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የተለያዩ ችግኞችን ለማዘጋጀት ታቅዶ ወደ ተግባር ተገብቷል ብለዋል። እስካሁንም በ65 ሺህ 694 የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ፣ ሀገር በቀልና የውጭ ዝርያ ችግኞችን ለማዘጋጀት የችግኝ መደቦችን በማዘጋጀት ዘር ማፍሰስ መቻሉን ገልጸዋል። ለአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር እየተዘጋጁ ካሉት ችግኞችም 1 ነጥብ 7 ቢሊዮኑ በተራቆቱ፣ ለደን ተከላ በሚለዩና በበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ በሚከናወንባቸው ተፋሰሶች እንደሚተከሉም አስረድተዋል። በክልሉ ባለፈው የክረምት ወቅት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተተከለው ከ1 ነጥብ 4 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መካከል በመጀመሪያ ዙር በተካሄደ ቆጠራ 86 ነጥብ 3 በመቶው ፀድቆ በመልካም ሁኔታ ላይ እንደሚገኝም ታውቋል።
በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማትና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ውጤታማ ናቸው
Dec 11, 2025 131
አዳማ፤ ታህሳስ 2/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማትና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። የዘንድሮውን የበጋ ወራት የተፋሰስ ልማትና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራን ስኬታማ ለማድረግ በየደረጃው የሚገኙ የዘርፉ ሙያተኞችና የስራ ኃላፊዎችን ያሳተፈ የቅድመ ዝግጅት መድረክ በአዳማ ገልመ አባገዳ አዳራሽ እየተካሄደ ነው። የቢሮው ኃላፊ ጌቱ ገመቹ በዚህ ወቅት እንደገለፁት ዘንድሮ የበጋ ወራት የአፈርና ውሃ ዕቀባ ስራ በትኩረት ይከናወናል። በክልሉ ባለፉት ሰባት ዓመታት የተከናወኑ የተፋሰስ ልማትና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን ገልፀው በዚህም የመሬት መራቆት፣ የአፈር መሸርሸር፣ የጎርፍና የድርቅ ስጋት መቀነሱን አስታውቀዋል። በተጨማሪም የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራው የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን ተፅዕኖ ለመቋቋም፣ ምርትና ምርታማነትን ለመጨመርና የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ አስተዋፅኦ እያበረከተ ይገኛል ብለዋል። በክልሉ ዓምና የእርከን ማሰር፣ የአፈርና ውሃ ዕቀባ፣ የተፋሰስና በአረንጓዴ ዐሻራ ፕሮግራም የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ተግባር መከናወኑን አስረድተዋል። ባለፉት ዓመታት በተሰሩ ስራዎችም የከርሰ እና ገፀ ምድር የውሃ ሀብት እየጨመረ መምጣቱን ጠቁመው የደረቁ ወንዞች፤ ጅረቶችና ሃይቆች መመለሳቸውን ተናግረዋል። በዚህም የበጋ መስኖ ስንዴን በበቂ የውሃ አቅርቦት ማልማት መቻሉን ገልጸው ለዓሣ ዕርባታና ለመጠጥ አገልግሎቶች እየዋሉ መሆኑንም ተናግረዋል። በተመሳሳይም ከሰውና እንስሳት ንኪኪ ነፃ ሆኖ ያገገመ መሬትን የደን ሀብቱን በመጠበቅ ለስራ ዕድል ፈጠራ ከማዋል ባለፈ ለንብ ማነብ ተግባር እየዋለ ይገኛል ብለዋል። በዘርፉ የተገኘውን ውጤት ይበልጥ አጠናክሮ ለማስቀጠል ዘንድሮ የአፈርና ውሃ ዕቀባና የተፋሰስ ልማት ስራውን ለማከናወን ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል። ለዚህም አምስት ሺህ 930 ተፋሰሶች መለየታቸውን ገልፀው በአፈርና ውሃ እቀባውና በተፋሰስ ልማት ስራው ዘጠኝ ነጥብ ስምንት ሚሊየን ህዝብን ለማሳተፍ በቂ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ መርኃ-ግብር ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በተግባር እያገዘ ይገኛል
Dec 11, 2025 161
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት እያገዘ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ፡፡ የከርሰ ምድር የውሃ አቅምን በማጎልበት የመስኖ እርሻዎች እንዲስፋፉ የበኩሉን ሚና እየተወጣ መሆኑም ተገልጿል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ተግባራዊ የተደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር በዓለም አቀፍ ደረጃ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ለሚደረገው ጥረት ትልቅ አስተዋጽዖ አበርክቷል፡፡ መርኃ-ግብሩ ለመጪው ትውልድ ተስፋ ብቻ ሳይሆን አሁን ያለውንም ትውልድ ተጠቃሚነት ያረጋገጠ ሲሆን በስራ ዕድል ፈጠራና የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ አኳያ የራሱን ጉልህ ሚና እየተወጣ ነው፡፡ በዚህም ኢትዮጵያ በብራዚል ቤለም በተካሄደው የዓለም የአየር ንብረት (COP-30) ጉባኤ ላይ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት (COP-32) ጉባኤን እንድታስተናግድ መመረጧ ይታወቃል። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማትና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈጻሚ እና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የብሄራዊ ቴክኒክ ኮሚቴ ጸሃፊ ፋኑሴ መኮንን፤ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር ኢትዮጵያ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ እያደረገች ላለችው ጥረት ተግባራዊ ምላሽ እየሰጠ ይገኛል ብለዋል፡፡ ባለፉት ሰባት ዓመታት ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች የተተከሉ ሲሆን አርባ በመቶ የሚሆኑት ለምግብነት የሚውሉ መሆናቸውንም ተናግረዋል፡፡ አረንጓዴ አሻራ የአፈር መሸርሸርን በመቀነስና ለምነትን በመጨመር የግብርና ምርታማነት እንዲሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ተናግረዋል። የከርሰ ምድር የውሃ አቅምን በማሳደግ የመስኖ እርሻዎች እንዲስፋፉም የበኩሉን ሚና እየተወጣ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት ለምግብነት አገልግሎት የሚውሉ አትክልትና ፍራፍሬዎችን ጨምሮ ሌሎች ችግኞች በስፋት የተተከሉ መሆናቸውን ጠቁመው፤ እነዚህም ለቤተሰብ የገቢ ምንጭና ለሥርዓተ ምግብ መሻሻልም ጉልህ ድርሻ ማበርከቱን ጠቅሰዋል፡፡ በአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር የተተከሉ ችግኞች ደን በመሆን ለማር ምርት ምቹ ሁኔታ በመፍጠር የንብ አናቢዎችን ተጠቃሚነት እያሳደጉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በበርካታ ዘርፎች ሰፊ የሥራ ዕድሎችን በመፍጠር በተለይም የወጣቶችንና የሴቶችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያሳደገ እንደሚገኝም አክለዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር ለድርቅ ተጋላጭ የሆኑና የተራቆቱ አካባቢዎች ወደ ምርታማነት እንዲለወጡ በማድረግ ለምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥ የራሱን አስተዋጾኦ እያበረከተ መሆኑን አመላክተዋል፡፡
በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ዘርፍ የስራ ዕድልን ለማስፋፋት የግሉ ዘርፍ ሚና የጎላ ነው
Dec 10, 2025 242
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ዘርፍ የስራ ዕድልን ለማስፋፋት የግሉ ዘርፍ ሚና የጎላ መሆኑን የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ገለጹ። የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ”አረንጓዴ ስራዎች የተሻለ ነገ” በሚል መሪ ሃሳብ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ፎረምና ባዛር ማካሄድ ጀምሯል። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ መንግሥት በመደመር እሳቤ በኢኮኖሚ የበለጸገች ኢትዮጵያን ለትውልዱ ለማስረከብ በርካታ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን አንስተዋል። ባለሃብቶችና ኢንተርፕራይዞች በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ዙሪያ ያላቸውን ፈጠራና የፋይናንስ አቅርቦት እንዲያሳድጉ ፣ በተለይም በታዳሽ ሃይል ላይ የሚውል ካፒታል ፈሰስ ማድረግ፣ የኢኮኖሚ ኢኒሸቲቮችን ማገዝና ግብርናውን ማዘመን ላይ እንዲሳተፉ አሳስበዋል፡፡፡ ከነዚህ መካከል የሀገሪቱን የአየር ንብረት ሁኔታ ታሳቢ ያደረገ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ስራ ተጠቃሽ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ሽግግር በግሉ ዘርፍ ኢንቨስትመንት፣ በአረንጓዴ ፈጠራ፣ ፋይናንስና ኢንተርፕርነርሺፕ ላይ የተመሰረተ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ በአረንጓዴ የኢኮኖሚ ዘርፍ የሚፈጠር የስራ ዕድል ለኢትዮጵያ ዕድገት ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው ተግባሩ ከስራ፣ክህሎትና ኢንተርፕራይዞች ጋር ከተጣመረ ዘርፉን በፍጥነት ለማሳደግ ያግዛል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ አረንጓዴ ኢኮኖሚን በመጠቀም የስራ እድል ፈጠራን ለማስፋፋት የያዘቸውን ግብ እንድታሳካ አጋር አካላት የጀመሩትን ጥረት አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጥሪ አቅርበዋል። በኢትዮጵያ የስዊድን ኤምባሲ ከፍተኛ የፕሮግራም ስራ አስኪያጅ የሆኑት ኒኮላ ኤሪክሰን አረንጓዴ የስራ ዕድል ፈጠራ ኢትዮጵያ በዘርፉ የጀመረችውን ሽግግር ለማገዝና የማይበገርና የተሰባጠረ ኢኮኖሚ ለመገንባት ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ ታዳሽ የሃይል አቅርቦትና ትራንስፖርት፣የአየር ብክለት ልቀት ቅነሳ፣የቆሻሻ አወጋገድ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ዘርፍ በማደግ ላይ የሚገኙ አማራጮች መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ ኢትዮጵያ ይህንን እውን ማድረግ የሚችል በእውቀት የበለጸገና ጠንካራ ወጣት ሃይል አላት ብለዋል፡፡
በምዕራብ ጎንደር ዞን የበጋ ወቅት የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ ተጀመረ
Dec 10, 2025 149
ገንዳውሃ፤ ታህሳስ 1/2018(ኦዜአ)፡- በምዕራብ ጎንደር ዞን በተለያዩ ተፋሰሶች የበጋ ወቅት የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ መጀመሩን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ ዛሬ በተጀመረው በዚሁ ሥራ ላይ የዞኑ የሥራ ኃላፊዎች፣ የመከላከያ ሰራዊት አባላት፣ የፌዴራል ፖሊስና ሌሎች የሕብረተሰብ ክፍሎች የተሳተፉ ሲሆን፤ ሥራው ለ30 ቀናት እንደሚቆይ ተነግሯል ፡፡ የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አንዳርጌ ጌጡ በወቅቱ እንደገለጹት፤ በዞኑ በአራት ወረዳዎችና ሶስት ከተማ አስተዳደሮች በሚተገበረው የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ 2ሺ 300 ሄክታር የተጎዳ መሬት ይለማል። ከዚህ ውስጥ በዛሬው ማስጀመሪያ ፕሮግራም በተለያዩ ቀበሌዎች 110 ተፋሰሶች ላይ መከናወኑን አንስተዋል። የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ተግባር በወል መሬቶችና በግል ይዞታዎች የሚሰራ ሲሆን፤በዚህም የውሃ እቀባ፣ እርከን ሥራና ሌሎች ተግባራት ይከናወናሉ ብለዋል። በዘመቻ በሚካሄደው በዚህ የልማት ሥራ ከ36 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን ለማሳተፍ ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን አስረድተዋል። አርሶ አደሮቹ የተፋሰስ ልማት ሥራዎቹን ቀጣይነት ያለው ቁጥጥርና ክትትል በማድረግ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታቸውን ለማጉላት በተለየው መሬት ላይ ዕፅዋቶች እንዲያለሙ እንደሚደረግ ገልጸዋል። በሰሜን ምዕራብ ዕዝ የ504ኛ ኮር ምክትል አዛዥ ብርጋዴር ጄኔራል ቾምቤ ወርቁ በበኩላቸው፤ ሰራዊቱ ሰላምና ዳር ድንበርን ከማስከበር በተጨማሪ በልማት ሥራዎች በመሳተፍ ለሀገር እድገት የድርሻውን እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል። በበጋ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ በተከናወነበት ሥፍራ ክረምት ላይ ችግኝ በመትከል የሚሳተፉ መሆኑንም ጠቁመዋል። በዞኑ የገንዳውኃ ዙሪያ አርሶ አደር አየነው ያሲን በሰጡት አስተያየት፤ ባለፉት ዓመታት በተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራ ላይ ተሳትፈው መልካም ውጤት በማየታቸው በዚህ ዓመት ሥራውን አጠናክረው መቀጠላቸውን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት በወል መሬት ላይ በተከናወነው እርከንና ችግኝ ተከላ ልማት አፈሩ ተሸርሽሮ ከጥቅም ውጭ የነበረ ስፍራ አገግሞ ለከብት መኖና የከርሰ ምድር ውሃን በማጎልበት ተጠቃሚ እንዳደረጋቸውም አውስተዋል። በበጋ የአፈርና ውሃ የጥበቃ ሥራዎች የለሙ ተፋሰሶች ምርታማነታቸውን ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው የገለጹት ሌላኛው አርሶ አደር የሱፍ ዳምጤ ናቸው።
ኢትዮጵያ ኮፕ- 32 እንድታስተናግድ መመረጧ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የሚያስችሉ ስራዎች ውጤታማነትን የሚያመላክት ነው
Dec 10, 2025 142
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 1/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤን (ኮፕ- 32) እንድታስተናግድ መመረጧ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የሚያስችሉ ስራዎች ውጤታማነትን የሚያመላክት መሆኑን በኢትዮጵያ የጀርመን ኤምባሲ ጉዳይ ፈጻሚ ፈርዲናንድ ቮን ዌይህ (ዶ/ር) ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአካባቢ ስነ-ምኅዳር ደኅንነት በማስጠበቅ ጉልህ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ይህን ተከትሎ ኢትዮጵያ በብራዚል ቤለም በተካሄደው የዓለም የአየር ንብረት (COP-30) ጉባኤ ላይ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት (COP-32) ጉባኤ ለማስተናገድ መመረጧ ይታወቃል። በኢትዮጵያ የጀርመን ኤምባሲ ጉዳይ ፈጻሚ ፈርዲናንድ ቮን ዌይህ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት በኢትዮጵያ በሀይድሮ የኤሌትሪክ ሀይል፣ አረንጓዴ አሻራና ሌሎች በአረንጓዴ ልማት በተሰሩ ስራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ተመዝግበዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም እያከናወነች የምትገኘው ተግባር ችግሩን ለመከላከል ያላትን ቁርጠኝነት እንደሚያመላክትም ተናግረዋል። በኢትዮጵያ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ዘርፍ ፣ በታዳሽ ሀይል እና በደን ልማት የተሰሩ ውጤታማ ስራዎች ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤን እንድታስተናግድ ለመመረጧ አስተዋጽኦ ማድረጉን ገልጸዋል። በሀገሪቱና በዓለም አቀፍ ደረጃ በተካሄዱ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤዎች ኢትዮጵያ የነበራት ጉልህ ተሳትፎ ለመመረጧ ካገዟት መስፈርቶቹ መካከል ተጠቃሽ መሆናቸውን ገልጸዋል። በጀርመን የልማት እቅድ የግብርና ዘርፍ ዋና ምስሶ መሆኑን ገልጸው፤ ለዘርፉ ውጤታማነት የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የሚከናወኑ ስራዎች ትኩረት ከሚደረግባቸው ስራዎች መካከል እንደሚገኙ ጠቅሰዋል። ጀርመን በኢትዮጵያ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎችን እየደገፈች እንደምትገኝ ገልጸው፤ ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
ረቂቅ አዋጁ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስራዎችን የበለጠ ውጤታማ ለማድረግ ጉልህ ጠቀሜታ ይኖረዋል
Dec 5, 2025 317
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 26/2018(ኢዜአ)፦የሥርዓተ ምህዳር አገልግሎት ክፍያ ረቂቅ አዋጅ የሀገሪቱን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስራዎች የበለጠ ውጤታማ ለማድረግ ጉልህ ጠቀሜታ እንደሚኖረው በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ ገለጹ። በሕዝበ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና አካባቢ ልማት እና የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴዎች የሥርዓተ ምህዳር አገልግሎት ክፍያ ረቂቅ አዋጅ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ይፋዊ ውይይት መድረክ አካሂደዋል። በምክር ቤቱ የፕላን በጀትና ፋይናንስ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ በዚሁ ወቅት፤ የሥርዓተ ምህዳር አገልግሎት ክፍያ በተለያዩ አሰራሮች ላይ መኖሩን ጠቅሰዋል፡፡ አንድ ወጥ በሆነ አሰራር፣ ዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችና ሀገሪቱ ከደረሰችበት ደረጃ ጋር በተጣጣመ መልኩ ረቂቅ አዋጁ መዘጋጀቱ አስፈላጊ ነው ሲሉ ተናግረዋል። የሀገሪቱን የበለጸገ የስነ ምህዳር ሀብት ዘላቂ በሆነ ወጥ አሰራር ለማጠናከር የአገልግሎት ክፍያ ስርዓቱ አስፈላጊ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የደን ልማቶች የግብርና ምርታማነትን በማጎልበት አረንጓዴ ልማቶችን የበለጠ ውጤታማ ያደርጋል ብለዋል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ለሊሴ ነሜ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ የተፈጥሮ ሀብቶችን ጥበቃና እንክብካቤን በማጠናከር አካባቢ ላይ የሚደርሰውን ጉዳትና የህብረተሰቡን ተጋላጭነት መቀነስ አስፈላጊ ነው። ረቂቅ አዋጁ ለመጀመሪያ ጊዜ መዘጋጀቱን ገልጸው፤ የተለያዩ ማህበረሰብ ክፍሎች አካባቢያቸውን በመጠበቃቸው ለአገልግሎታቸው ክፍያ እንዲያገኙ የሚያደርግ የማበረታቻ ስርዓት የሚዘረጋ ነው ብለዋል። ስነ ምህዳር ላይ ጉዳት የሚያደርሱ እንቅስቃሴዎችን ለመከላከል የአካባቢን ጥበቃ በዘላቂነት የሚያበረታታ ሂደትን የሚፈጥር አዋጅ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በውይይቱ ላይ የተገኙ ባለ ድርሻ አካላት የስነ ምህዳር አገልግሎት አቅራቢዎች፣ ረቂቅ አዋጁ ላይ መካተት የሚገባቸውን ጉዳዮች፣ ግልጽነትን የሚጠይቁና ከትርጉም ጋር በተያያዘ ጥያቄዎችን አቅርበዋል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ለሊሴ ነሜ በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ፤በረቂቅ አዋጁ የስነ ምህዳር አገልግሎት ክፍያ ላይ የማህበረሰቡና የባለ ድርሻ አካላት ተጠቃሚነት፣ ተሳታፊነትና ፍትሃዊነት በግልጽ መቀመጡን ተናግረዋል። አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮች፣ የመንግስት ተቋማትና ሌሎች ባለ ድርሻ አካላት አገልግሎት አቅራቢዎች ይሆናሉ ብለዋል። ከግብርናና ከደን ልማት ጋር ተያይዞ የስነ ምህዳር አገልግሎት ክፍያ አስገዳጅ የሆነባቸው አዋጆች መኖራቸውን ጠቅሰው ረቂቅ አዋጁ የክፍያ ስርዓት ለመዘርጋት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የፌደራልና የክልል ባለ ድርሻ አካላትን ሚና እና ሀላፊነትም በግልጽ አስቀምጧል ብለዋል። በምክር ቤቱ የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና አካባቢ ልማት ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር)፤ በረቂቅ አዋጁ ላይ አሻሚ ትርጉም የሚሰጡ፣ ግልጽነት የጎደላቸው ጉዳዮች ተሻሽለው ጠንካራ አዋጅ እንዲወጣ በጋራ እንሰራለን ብለዋል።