አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ሁሉም በንቃት በመሳተፍ አሻራውን ሊያኖር ይገባል
Jul 5, 2025 45
ሶማሌ፤ ሰኔ 28/2017 (ኢዜአ)፡- በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ሁሉም በንቃት በመሳተፍ አሻራውን ሊያኖር ይገባል ሲሉ የሶማሌ ክልል ርእሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ ገለጹ። የክልሉ የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት እና አረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ርእሰ መስተዳድሩ በተገኙበት በጅግጅጋ ከተማ ተካሂዷል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ንግግር ያደረጉት የሶማሌ ክልል ርእሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ፤ በክልሉ የአረንጓዴ አሻራ ልማትን ጨምሮ በተከናወኑ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን ገልጸዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ባለፉት አመታት በተከናወኑ ስራዎች አካባቢን በመጠበቅና የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ሂደት ስኬቶች መታየታቸውን አንስተዋል። በመሆኑም በዘርፉ ልማት ዘንድሮም ዝግጅት መደረጉን ገልጸው በመርሃ ግብሩ ሁሉም በነቂስ በመሳተፍ አሻራውን እንዲያሳርፍ አስገንዝበዋል። ከችግኝ ተከላ በተጨማሪ በክረምት በጎ ፈቃድ የአረጋውያንና አቅመ ደካሞችን ቤት በማደስና በመገንባት፣ በአካባቢ ጥበቃ፣በደም ልገሳ እና ሌሎችም መስኮች ነፃ አገልግሎቱ እንዲጠናከር አፅእኖት ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ሰኔ 20 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ በይፋ ማስጀመራቸው ይታወቃል።
የአረንጓዴ አሻራ ልማትን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በተግባር የተገነዘብን በመሆኑ ችግኞችን ለመትከል እና ለመንከባከብ ተዘጋጅተናል
Jul 5, 2025 60
አሶሳ፤ ሰኔ 28/2017 (ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ ልማትን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በተግባር የተገነዘብን በመሆኑ ችግኞችን ለመትከል እና ለመንከባከብ ተዘጋጅተናል ሲሉ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ የተሳተፉ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተናገሩ። የ2017 የአረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር በክልሉ በኡራ ወረዳ ሰልጋ 20 ንዑስ ተፋሰስ ልማት ላይ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን በተገኙበት በይፋ ተጀምሯል። በመርሃ ግብሩ ላይ ከተገኙት መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የአረንጓዴ አሻራ ልማትን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በተግባር የተገነዘብን በመሆኑ ችግኞችን ለመትከል እና ለመንከባከብ ተዘጋጅተናል ብለዋል። ካነጋገርናቸው መካከል አቶ አብዱላሂ ሙሀመድ እና ወይዘሮ ሺዋጋ አለሙ፤ የአረንጓዴ አሻራ ውጤት ምግብም፣ ጥላና ከለላም እየሆነ እኛንም ተፈጥሮንም እየጠበቀ ይገኛል ሲሉ ተናግረዋል። በአካባቢያቸው መሬት እንዲያገግም እና ለእንስሳት መኖ በቅርበት እንዲያገኙ እያደረገም ስለመሆኑ አንስተዋል። በተለይም በተፋሰስ ልማት ላይ የሚተከሉ ችግኞች የመጽደቅ መጠናቸው ከፍተኛ በመሆኑ የተፋሰስ ልማት እና የችግኝ ተከላን በተጠናከረ መልኩ የሚያስቀጥሉ መሆኑን አረጋግጠዋል። ሌላው በመርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉት መቶ አለቃ በሱፍቃድ ገላን፤ የመከላከያ ሰራዊት የሀገርን ዳር ድንበር ከማስጠበቅ ባለፈ በተለያዩ የልማት ስራዎች ላይ የነቃ ትብብርና ተሳትፎ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም መሰረት የልማት አጋር በመሆን በዛሬው እለት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሻራቸውን ማኖራቸውን ገልጸዋል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የተሳተፈችው ተማሪ ፎዚያ ሙሀመድ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለትውልድ የሚተርፍ አሻራ በመሆኑ የዚሁ ታሪክ አካል ለመሆን ተገኝቻለሁ ብላለች። በመርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ርእሰ መስተዳደር አሻድሊ ሀሰንን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች፣ የፀጥታ አካላት እና የአካባቢው ማህበረሰብ ክፍሎች ተገኝተው አሻራቸውን አኑረዋል።
በለውጡ ዓመታት ለአረንጓዴ አሻራ ልማት የተሰጠው ትኩረት የተራቆቱ አካባቢዎችን እየለወጠ ነው- አቶ አሻድሊ ሃሰን
Jul 5, 2025 50
አሶሳ፤ ሰኔ 28/2017(ኢዜአ)፦በለውጡ ዓመታት ለአረንጓዴ አሻራ ልማት የተሰጠው ትኩረት የተራቆቱ አካባቢዎችን እየለወጠ እንደሚገኝ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሃሰን ገለጹ። በክልሉ እየተከናወነ ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የህዳሴ ግድብን ከደለል በመከላከል ረገድ ፋይዳው የላቀ መሆኑንም ርዕሰ-መስተዳድሩ ተናግረዋል። ዛሬ በክልሉ ኡራ ወረዳ ሰልጋ 20 ንዑስ ተፋሰስ ልማት ላይ በተከናወነው የ2017 የአረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ላይ ርዕሰ-መስተዳድሩ እንደገለጹት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ከተጀመረ በኋላ በአካባቢው ስነ-ምህዳር ተጨባጭ ለውጥ መጥቷል። በክልሉ እየተከናወነ ያለው ተከታታይ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ከልማትም ባለፈ የህዳሴ ግድብን ከደለል በመከላከል ረገድ ፋይዳው የላቀ መሆኑን ገልጸዋል። በለውጡ ዓመታት በተለይም ለአረንጓዴ አሻራ ልማት በተሰጠው ልዩ ትኩረት በርካታ የተራቆቱ አካባቢዎች እየለሙ መሆኑን አንስተዋል። ባለፉት ዓመታት የተተከሉ የኢኮኖሚ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ፍሬ እየሰጡ በመሆኑ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥና የአካባቢ ጥበቃን በማጠናከር ውጤት መጥቷል ሲሉም ተናግረዋል። የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ የተጀመረ ሲሆን በክልሎችም በተጠናከረ መልኩ ቀጥሏል። በመሆኑም በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልም በዛሬው እለት በይፋ መጀመሩን ተከትሎ የክልሉ ህዝብ በትጋት አረንጓዴ አሻራውን ለማሳረፍ እንዲነሳሳ ርእሰ-መስተዳድሩ ጥሪ አቅርበዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ ባበክር ሀሊፋ፤ በክልሉ አብዛኛው ተፋሰሶች ከህዳሴ ግድብ ጋር የሚያያዙ በመሆናቸው የሚተከሉ ችግኞች ህዳሴ ግድብን ከደለል ለመጠበቅ ፋይዳቸው የጎላ ነው ብለዋል። እስከ አሁን በ47 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ሲከናወን መቆየቱን የገለፁት ኃላፊው የተፋሰስ ልማት በተከናወነበት አካባቢ ደግሞ ችግኞች በብዛት የሚተከሉ መሆኑን ተናግረዋል። በችግኝ ተከላ መርሃ-ግብሩ በየደረጃው ያሉ የክልሉ አመራሮች፣ የፀጥታ አካላት፣ ወጣቶች እንዲሁም የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
የአረንጓዴ አሻራ ልማቱ እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመውጣት ለሚደረገው ጥረት ፋይዳው የላቀ ነው
Jul 5, 2025 51
ጋምቤላ ፤ ሰኔ 28/2017 (ኢዜአ) ፦የአረንጓዴ አሻራ ልማቱ እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመውጣት ለሚደረገው ጥረት ፋይዳው የላቀ መሆኑን የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። ''በመትከል ማንሰራራት'' በሚል መሪ ሀሳብ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ በይፋ የተጀመረው የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በክልሎችም ተጠናክሮ ቀጥሏል። በዚህም በዛሬው እለት በጋምቤላ የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድ፤ በተገኙበት በክልል ደረጃ የአረንጓዴ አሻራ ልማት በይፋ ተጀምሯል። ርዕሰ መስተዳድሯ አሻራቸውን ካኖሩ በኋላ ባስተላለፉት መልእክት የአረንጓዴ አሻራ ልማቱ እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመውጣት ለተጀመሩ ጥረቶች ጉልህ ድርሻ አለው ብለዋል። በዚህም መሰረት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሩ በክልሉ በተጠናከረ መልኩ መቀጠሉን አንስተው በልማቱ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በብዛት የሚተከሉ መሆኑን ተናግረዋል። ከመትከልም ባለፈ ለጽድቀታቸው በመንከባከብና በመጠበቅ ለአገልግሎት እንዲበቁ ማድረግ የሁሉም አደራና ሃላፊነት እንዲሆን ርእሰ መስተዳድሯ ጠይቀዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ፓል ቱት፤ የአረንጓዴ አሻራ ልማቱ የአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነትን ለመቀነስና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ ባለፉት ተከታታይ አመታት በተከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ልማት በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት አጋዥ መሆኑንም ተናግረዋል። በዚህ ዓመት ለተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች 60 በመቶ የሚሆኑት የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ጠቁመው ከ7 ሺህ ሄክታር በላይ የተራቆቱ መሬቶችን በስነ-ህይወት የማላበስ እቅድ ተይዟል ብለዋል። በዛሬው እለይ በይፋ የተጀመረው ክልል አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ለቀጣይ ሁለት ወራት ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑም ታውቋል።
በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራዎች ዘርፈ ብዙ ለውጦች ተመዝግበዋል-ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር )
Jul 5, 2025 46
ሼይ ቤንች፤ ሰኔ 28/2017(ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራዎች ዘርፈ ብዙ ለውጦች መመዝገባቸውን ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ። የዘንድሮ ክልል አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ዛሬ በቤንች ሸኮ ዞን ሼይ ቤንች ወረዳ ተካሂዷል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንደገለጹት ላለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራዎች ዘርፈ ብዙ ውጤቶች ተመዝግብዋል። የአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራ በክልሉ የአየር ጸባይ ለውጥን ለመቋቋም፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃን ለማጠናከር እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጉልህ አስተዋጽኦ እያደረገ መሆኑን በማሳያነት ጠቅሰዋል። የአረንጓዴ ልማት ሥራው በክልሉ ያለውን ደን የመጠበቅ እና የመንከባከብ ባህልን በሚያጠናክር መልኩ እየተተገበረ መሆኑን ጠቁመው፣ ይህም ከአረንጓዴ አሻራ ልማት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማስቀጠል ያስችላል ብለዋል። የክልሉ ህዝብ ለልማት ሥራው ያለውን ቁርጠኝነት አጠናክሮ በማስቀጠል ለክልሉ ለውጥና ዕድገት ተግቶ እንዲሰራ ጠይቀዋል። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው በበኩላቸው በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተተከሉ ችግኞች እየታዩ ያሉ ለውጦችን ለማጠናከር ይሰራል ብለዋል። እንደ ሃላፊው ገለጻ በስድስት ዙሮች ከተተከሉ የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ውስጥ ከ86 በመቶ በላይ ጸድቀዋል። ዘንድሮ የቡና፣ የፍራፍሬ እና የደን ዛፍ ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱንም ገልጸዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የመሬት ለምነትን በማሳደግ፣ አፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራን በማጠናከር ለምርትና ምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ያሉት ደግሞ የቤንች ሸኮ ዞን ምክትል ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሀብታሙ ካፍትን ናቸው። በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ ለፍራፍሬ ልማት ትኩረት መሰጠቱ በምግብ ራስን ለመቻል የሚደረገውን ጥረት ያግዛል ብለዋል። በሼይ ቤንች ወረዳ ጋያሸማ ቀበሌ ዛሬ በይፋ በተጀመረው ክልላዊ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች እና የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ የተተከሉ እጽዋቶችን ተንከባክቦ ለውጤት የማብቃቱ ተግባር ይጠናከራል
Jul 5, 2025 44
ሐረር ፤ ሰኔ 28/2017 (ኢዜአ)፡- በሐረሪ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ እጽዋቶችን ተንከባክቦ ለውጤት የማብቃቱ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ እና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች በጀጎል ዙሪያ የተተከሉ እጽዋቶችን የመንከባከብ ስራ አከናውነዋል። በዚህ ወቅት ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር ሰጪነት የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በክልሉም በመተግበር ባለፉት ዓመታት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው በርካታ እጽዋቶች መተከላቸውን አስታውሰዋል። በመርሃ ግብሩ የተተከሉ ችግኞች አካባቢን አረንጓዴ ከማላበስ ባለፈ ውብና ማራኪ እንዲሁም ለነዋሪውና ቱሪስት ምቹ እንዲሆኑ እያስቻለ መምጣቱንም ተናግረዋል። የተተከሉ እጽዋቶችን በቅርበት በመከታተልና በመንከባከብ ለውጤት የማብቃቱ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል።ይህም ጤናማና ጽዱ ስፍራዎችን ማበልጸግ መሆኑን ጠቁመዋል። ርዕሰ መስተዳድሩ ፤ ማህበረሰቡም ሆነ ተቋማት የተከሏቸውን ችግኞች የመንከባከብና ውሃ የማጠጣት ስራ በማከናወን የድርሻችንን መወጣታችንን ማጎልበት አለብን ብለዋል። በቀጣይ ቀናት "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መሪ ሃሳብ በክልሉ ከተማና ገጠር ወረዳዎች በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው ችግኝ የመትከልና ቀደም ሲል የተተከሉትን የመንከባከብ ስራ እንደሚከናወንም ጠቁመዋል። በተለይ በመርሃ ግብሩ ላይ በመሳተፍ ቀደም ሲል የተተከሉ እጽዋቶችን ሲንከባከቡ ለቆዩ የፖሊስ አባላት፣ወጣቶችና ሌሎችም የሕብረተሰብ ክፍሎች ምስጋና አቅርበዋል። ዛሬ ከጠዋቱ 12 ጀምሮ በተከናወነው የተተከሉ እጽዋቶች እንክብካቤ ላይ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ሮዛ ኡመር፣ የክልሉ ካቢኔ አባላት፣የጸጥታ ሃይል፣የመንግስት ተቋማት ሰራተኞችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በክልሉ ለአረንጓዴ አሻራ ልማት መጠናከር ህብረተሰቡ ሲያከናውን የቆየውን ተግባር ማጠናከር አለበት
Jul 4, 2025 79
ሚዛን አማን፣ሰኔ 27/2017 (ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ለአረንጓዴ አሻራ ልማት መጠናከር ህብረተሰቡ በቁርጠኝነት ሲያከናውን የቆየውን ተግባር አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተገለጸ። የክልሉ የ2017 ዓ.ም የክረምት ወራት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ነገ በይፋ እንደሚጀመር ተመላክቷል። በክልሉ ውስጥ የሚገኙ የብሔራዊና የክልል ሚዲያ ተቋማት አመራሮችና ባለሙያዎች ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ጋር በመሆን በሚዛን አማን ከተማ ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ በረከት እዮብ በእዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ የዘንድሮ የክልሉ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ነገ በይፋ የሚጀመር ሲሆን አስፈላጊው ዝግጅትም ተደርጓል። በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች እንደሚተከሉም አስታውቀዋል። ለዚህም የችግኝና የጉድጓድ ቁፋሮ ዝግጅት ተደርጓል ያሉት ወይዘሮ በረከት፣ በዛሬው እለትም የመገናኛ ብዙሀንና የኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን ማሳረፋቸውን ተናግረዋል። በክልሉ ለአረንጓዴ አሻራ ልማት መጠናከር ህብረተሰቡ በቁርጠኝነት ሲያከናውን የነበረውን ተግባር በቀጣይም አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ወይዘሮ በረከት ገልጸዋል። በክልሉ ባህል ሆኖ የቆየውን የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ለማስቀጠልና የራስን አሻራ አክሎ ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ በሚደረግ ጥረት ህብረተሰቡ ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ ሲያደርግ የቆየውን ተሳትፎ እንዲያጠናክርም አሳስበዋል። ዛሬ በተካሄደው የመገናኛ ብዙሀን ባለሙያዎች የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ላይ የተሳተፉት የደቡብ ሬዲዮና ቴሌቭዥን ድርጅት ሚዛን ቅርንጫፍ ሥራ አስኪያጅ አቶ ትዕዛዙ ኬንጫ፣ ከዘገባ ሥራ ባሻገር አረንጓዴ አሻራችንን በማሳረፍ ልማቱን ለማጠናከር በችግኝ ተከላው ላይ መሳተፋቸውን ገልጸዋል። በጋራ ችግኝ በመትከላቸው ደስተኛ መሆናቸውን ገልጸው፣ ህብረተሰቡ የችግኝ ተከላ ተሳትፎውን በማጠናከር የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ግብን ለማሳካት መረባረብ ይኖርበታል ብለዋል። የመገናኛ ብዙሀን ባለሙያዎች ችግኝ በመትከል የአረንጓዴ አሻራቸውን በማሳረፍ የዜግነት ግዴታቸውን እንዲወጡ መደረጉ መልካም ነው ያለው ደግሞ የቤንች ሸኮ ዞን ኮሙኒኬሽን ባለሙያ ተዘራ ጥላሁን ነው። መሰል መርሃ ግብሮች ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ገልጾ፣ "የክልሉ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ቢሮ በዚህ መልኩ አቀናጅቶ ችግኝ እንድንተክል ማድረጉ ይበረታታል" ብሏል። በሚዛን አማን ከተማ በተካሄደው የመገናኛ ብዙሀን ተቋማት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ላይ የተለያዩ መገናኛ ብዙሀን ባለሙያዎች፣ የኮሙኒኬሽን ሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል። "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መሪ ቃል ክልል አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሀግብር ነገ በቤንች ሸኮ ዞን ሸይ ቤንች ወረዳ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት እንደሚካሄድ ታውቋል።
በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተከላ የተዘጋጁ ችግኞችን በሳይንሳዊ መንገድ በመትከል እንዲጸድቁ ማድረግ ያስፈልጋል - የግብርና ሙያተኞች
Jul 4, 2025 78
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2017(ኢዜአ)፦በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተከላ የተዘጋጁ ችግኞችን በሳይንሳዊ መንገድ በመትከል እንዲጸድቁ ማድረግ እንደሚያስፈልግ የዘርፉ የግብርና ሙያተኞች አስገነዘቡ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በዜጎች የነቃ ተሳትፎ ያለፉት ሰባት ዓመታት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሀገርን የደን ሽፋን በማሳደግ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ በማበርከት ላይ ይገኛል። የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሰኔ 20 ቀን 2017 ዓ.ም "በመትከል ማንሰራራት'' በሚል መሪ ሃሳብ 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ የመትከል ግብን አስጀምረዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎትም በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞችን የጽድቀት መጠን ለማሳደግ ሊደረጉ የሚገባቸውን የተከላ ጥንቃቄ ሥርዓት በሚመለከት የዘርፉን ሙያተኞች አነጋግሯል። በግብርና ሚኒስቴር የሥነ-ሕይወታዊ የአፈርና ውሀ ጥበቃና ጥምር ደን እርሻ ዴስክ ኃላፊ በፍቃዱ ብርሃኔ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቀነስ ጉልህ ፋይዳ አለው ብለዋል። በተያዘው ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም ኢትዮጵያዊያን ችግኞችን በሳይንሳዊ መንገድ በጥንቃቄ በመትከል ለታለመላቸው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዓላማ ማዋል እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት የልማት አጀንዳ ነው ያሉት ኃላፊው፤ በተከላ ወቅትም ላስቲኮችን አንስቶ መትከልና የተቆፈረውን አፈር በአግባቡ ወደ ቦታው መመለስ ይገባል ብለዋል። በአዲስ አበባ የከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ የተፋሰስና አረንጓዴ ልማት ዳይሬክተር ስንታየሁ መንግስቱ እንደገለጹት፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚሳተፉ ዜጎች ችግኞችን በጥንቃቄ መትከል ይኖርባቸዋል። በመርሃ ግብሩ የሚተከሉ ችግኞችን የጽድቀት መጠን ማሻሻል በሚያስችል መንገድ የነቃ ተሳትፎ በማድረግ አሻራቸውን ማሳረፍ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተፋሰስ ልማት ስራ የተዘጋጁ ጉድጓዶች ያቆሩትን ውሃ በማፋሰስ ለሚተከሉ ችግኞች ጽድቀት በትኩረት መስራት እንደሚያስፈልግ መልዕክት አስተላልፈዋል። በግብርና ሚኒስቴር የሥነ-ሕይወታዊ የአፈርና ውሀ ጥበቃና ጥምር ደን እርሻ ዴስክ ኃላፊ በፍቃዱ ብርሃኔ÷ ዜጎች በችግኝ ተከላ የሚያደርጉትን የነቃ ተሳትፎ ተንከባክቦ በማጽደቅ መድገም ይኖርባቸዋል ብለዋል። የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬታማ ለማድረግ ለህብረተሰቡ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ ተሰርቷል ያሉት ደግሞ በአዲስ አበባ የከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ የተፋሰስና አረንጓዴ ልማት ዳይሬክተር ስንታየሁ መንግስቱ ናቸው።
ተማሪዎች በሀገር ልማት ላይ ያላቸውን ተሳትፎ ሊያጠናክሩ ይገባል -ርዕሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድ
Jul 3, 2025 178
ጋምቤላ ፤ ሰኔ 26/2017 (ኢዜአ)፡- ተማሪዎች በሀገር ልማት ላይ ያላቸውን ተሳትፎ ሊያጠናክሩ ይገባል ሲሉ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድ ገለፁ። በጋምቤላ ዩኒቨርስቲ በመጀመሪያው ዙር የ12ኛ ክፍል የብሔራዊ ፈተና የወሰዱ ተማሪዎች ርዕሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድን ጨምሮ ከክልሉ ከፍተኛ አመራሮችና ከጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ ጋር የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሂደዋል። ርዕሰ መስተዳድሯ አለሚቱ ኡሞድ፣ በችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ላይ እንዳሉት ተማሪዎች በሀገሪቱ የልማት ስራዎች ላይ ያላቸውን ተሳትፎ ማጠናከር ይጠበቅባቸዋል። መንግስት የሀገሪቱን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ልማቶች ለማሳደግ በሚያደረገው ጥረት የተማሪዎች ድርሻ ከፍተኛ መሆኑንም ተናግረዋል። ዛሬ በጋምቤላ ዩኒቨርስቲ የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና ከወሰዱ ተማሪዎች ጋር የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብርም ይህንኑ ለማጠናከር ያለመ መሆኑን ገልፀዋል። ተፈታኝ ተማሪዎችም በክረምቱ የእረፍት ጊዜያቸው የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች ላይ በንቃት በመሳተፍ የአካባቢያቸውን ህዝብ ማገልገል እንደሚኖርባቸው አስገንዝበዋል። የጋምቤላ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንት ድሪባ ኢቲቻ (ዶ/ር) በቡኩላቸው የ2017 የትምህርት ዘመን የመጀመሪያው ዙር የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና በስኬት መጠናቀቁን ተናግረዋል። ተፈታኝ ተማሪዎቹም ከክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በዩኒቨርስቲው ግቢ ውስጥ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ ማከናወናቸው በሀገር ልማት አሻራቸውን የሚያሳርፉበትን እድል ማስፋቱን ገልፀዋል። ከተፈጥሮ ሳይንስ ተፈታኞች መካከል ተማሪ ላትጆር ቱትና ተማሪ ኮንግ ጆክ በሰጡት አስተያየት ከክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ጋር የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ ላይ መሳተፋቸው ለሀገራቸው እድገት የበኩላቸውን ሚና የሚያበረክቱበትን አጋጣሚ መፍጠሩን ጠቁመዋል። ዛሬ በጋምቤላ ዩኒቨርስቲ የጀመሩቱን የአረንጓዴ አሻራ ልማት ወደ መጡበት አካባቢ ሲመለሱም ወጣቶችን በማስተባበር አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስረድተዋል።
በአማራ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል
Jul 2, 2025 152
ባህርዳር ሰኔ 25/2017 (ኢዜአ) ፡-በአማራ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መዘጋጀታቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት፤ ለክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተደረገውን አጠቃላይ ዝግጅት በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በማብራሪያቸውም በክልሉ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርጋ ግብር ከ1 ነጥብ 5 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ከእነዚህ መካከል 20 ሚሊዮን የሚሆነው የቡና እና ለምግብነት የሚውሉ የተለያዩ የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውንም ተናግረዋል። ለችግኝ ተከላው ቀደም ብሎ መሬት በመለየት የጉድጓድ ቁፋሮ እና ሌሎች አስፈላጊ ዝግጅቶች መደረጋቸውን አንስተው ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል አሻራውን ለማኖር እንዲዘጋጅ ጥሪ አቅርበዋል። የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ልማት በሀገር አቀፍ ደረጃ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዲስ አበባ በይፋ መጀመሩን ተከትሎ በአማራ ክልልም ተጀምሯል። በክልሉ በአዊ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞንና በባህርዳር ከተማ አስተዳደር የችግኝ ተከላ መከናወኑን አስታውሰው በሌሎች አካባቢዎችም በተጠናከረ መልኩ ይቀጥላል ብለዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የሰከላ ወረዳ አርሶ አደር ገደፋዬ ሞገስ እና በአዊ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን የጓጉሳ ወረዳ አርሶ አደር አለማሁ አድማስ፤ የተራቆቱ አካባቢዎችን በመትከልና በመንከባከብ የድርሻችንን ለመወጣት ተዘጋጅተናል ሲሉ ተናግረዋል። ጥቅሙን በአግባቡ በመረዳቸው በዘንድረው የክረምት ወቅትም የሚተክሏቸውን ችግኞች በባለቤትነት ተንከባክበው ለማሳደግ መዘጋጀታቸው አስታውቀዋል። በክልሉ ባለፈው ዓመት የክረምት ወቅት ከተተከሉት ከ1 ነጥብ 4 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ከ82 በመቶ በላይ መፅደቁን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የአገሪቱ አካባቢዎች ከቀላል እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ-ኢንስቲትዩቱ
Jul 2, 2025 98
አዲስ አበባ፤ሰኔ 25/2017(ኢዜአ):-በሚቀጥሉት አስር ቀናት የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የአገሪቱ አካባቢዎች ብዙ ቦታዎች ላይ ከቀላል እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው በሚቀጥሉት አስር ቀናት ለክረምት ዝናብ መፈጠር ምቹ ሁኔታን የሚፈጥሩ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች ይበልጥ እየተስፋፉና እየተጠናከሩ ይቀጥላሉ። በደቡብ ምዕራብ፣ምዕራብ፣ሰሜን ምዕራብ፣ሰሜን፣ መካከለኛው እና ሰሜን ምስራቅ የአገሪቱ ክፍሎች ላይ የተሻለ የዝናብ መጠንና ሥርጭት እንደሚኖር አሃዛዊ የትንበያ መርጃዎች እንደሚያሳዩ ተጠቁሟል። በተለይ በደቡብ ምዕራብ፣ ምዕራብ፣ ሰሜን፣ ሰሜን ምዕራብና መካከለኛ የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ ከቀላል እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ያገኛሉ ብለዋል። አልፎ አልፎ በውሃ አካላትና አካባቢ በምዕራብ፣ሰሜን ምዕራብ፣ ሰሜን ምስራቅ እና መካከለኛው የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ በ24 ሰዓት ውስጥ ከ30 ሚሊ ሜትር በላይ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ሊኖራቸው እንደሚችል ገልጸዋል። በተወሰኑ አካባቢዎች ላይ ነጎድጓዳማና በረዶ አዘል ዝናብ እና የዝናቡ ጥንካሬም ለረጅም ሰዓታት ያለማቋረጥ ዝናብ ሊኖር እንደሚችል በመግለጫው ተመላክቷል። በክረምቱ ወቅት የሚዘንበው ዝናብ በአመዘኙ አዎንታዊ ሚና የሚኖረው መሆኑ ተገልጿል። ይህም አስቀድሞ ለተዘሩ ሰብሎች፣ ለመኽር ሰብሎች፣ ለቋሚ ተክሎችና የጓሮ አትክልት የውሃ ፍላጎት ለማሟላት በኩል መልካም አጋጣሚ የሚፈጥር መሆኑ ተገልጿል። አብዛኛው የአገሪቱ ተፋሰሶች ላይ ከመጠነኛ እስከ ከፍተኛ የገጸ ምድር የውሃ ፍሰት ይኖራቸዋል፤ነገር ግን አልፎ አልፎ የሚኖረው ከባድ ዝናብ ጎርፍ ሊያስከትል ስለሚችል ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ ተመላክቷል። በሌላ በኩል በመጪው አስር ቀናት የቀኑ ከፍተኛ ሙቀት በአፋር፣ በምስራቅ አማራ፣ በሰሜን ምዕራብ፣ምዕራብ እና ደቡብ ምስራቅ የአገሪቱ ሥፍራዎች ላይ ከ26 እስከ 41 ዲግሪ ሴልሺዬስ በላይ ሙቀት እንደሚኖራቸው ትንበያው ያሳያል።
በአረንጓዴ አሻራ በንቃት በመሳተፍ ሌሎች የማህብረሰብ ክፍሎች ተሳትፏቸውን እንዲያጠናክሩ እንሰራለን -የምክር ቤት አባላት
Jul 2, 2025 90
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2017(ኢዜአ)፦በእረፍት ጊዜያቸው ወደ ተመረጡበት አካባቢ ሲሄዱ በአረንጓዴ አሻራ በንቃት በመሳተፍ ሌሎች የማህብረሰብ ክፍሎች ተሳትፏቸውን እንዲያጠናክሩ አበክረው እንደሚሰሩ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ሰኔ 20/2017 ዓ.ም በይፋ ማስጀመራቸው ይታወቃል። "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መሪ ሃሳብ በሚካሄደው በዘንድሮው አረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በአገር አቀፍ ደረጃ 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ይሆናል። ይህንን ተከትሎ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር መካሔድ ጀምሯል። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት አረንጓዴ አሻራን አስመልክቶ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየትም ዜጎች በአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር በመሳተፍ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚደረገውን ጥረት የበኩላቸውን እየተወጡ ይገኛሉ። ዜጎች በአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር እያደረጉ ያለውን ተሳትፎ የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡ አባላቱ በእረፍት ጊዜያቸው ከማህበረሰቡ ጋር በመሆን በአካባቢያቸው በአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር የነቃ ተሳትፎ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል አዲሷ አሰፋ እንደገለጹት፤ ችግኝ መትከል ከሚሰጠው ዘርፈ ብዙ ጥቅም በተጨማሪ ለምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥ ትልቅ ጠቀሜታ አለው፡፡ በመሆኑም ማህበረሰቡ በአረንጓዴ አሻራ ላይ ያለውን ተሳትፎ ይበልጥ በማጠናከር ውጤቱን ማሳደግ እንደሚገባም አመልክተዋል፡፡ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሀብት ልማት ስራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል ኡስታዝ ካሚል አሊ በበኩላቸው፤ አረንጓዴ አሻራ ለሁለንተናዊ አገራዊ እድገት ወሳኝ በመሆኑ ዜጎች በአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር ላይ ተሳትፏቸውን ማጠናከር አለባቸው ብለዋል፡፡ በዚህ ረገድ በቀጣይ ወደ ተመረጡበት አካባቢያቸው ሲመለሱ ከተጣለባቸው ኃላፊነት ጎን ለጎን ህዝቡ በአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር ይበልጥ ተሳትፎ እንዲጠናከር እንደሚሰሩ ገልጸዋል። በምክር ቤቱ የህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል ወጌ ቁፋ አረንጓዴ አሻራ ቀደም ሲል በኢትዮጵያ ተመናምኖ የቆየውን የደን ሃብት ወደ ነበረበት በመመለስ ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ አበርክቷል ብለዋል። በመሆኑም ህዝቡ በአረንጓዴ አሻራ ላይ ያለውን ተሳትፎ እንዲጨምር ህዝቡን በማስተባበርና አብሮ በመትከል አገራዊ ሃላፊነታቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። ባለፉት አመታት በተከታታይ ተግባራዊ በተደረገው በአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር እየተገኙ ያሉ ውጤቶችን ዘላቂ ማድረግ የሁሉም ዜጋ ሃላፊነት ነው ያሉት ደግሞ በምክር ቤቱ የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል ሙሉነሽ ነሞሬ ናቸው። በመሆኑም ማህበረሰቡ ለአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር ያለውን ተነሳሽነት በመጨመር ያለውን ተሳትፎ እንዲያጎላ ጥሪ አቅርበዋል።
የአካባቢ መራቆት የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቋቋም ችግኝ ከመትከል ባለፈ ለእንክብካቤ ሥራ ትኩረት ሰጥተናል
Jul 2, 2025 79
ወሊሶ፤ ሰኔ 25/2017(ኢዜአ)፡-የአካባቢ መራቆት የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቋቋም ችግኝ ከመትከል ባለፈ ለእንክብካቤ ሥራ ትኩረት መስጠታቸውን ኢዜአ ያነጋገራቸው የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ዞን ነዋሪዎች ገለጹ። በኦሮሚያ ክልል ደረጃ የዘንድሮው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ዞን ወንጪ ወረዳ የክልሉ መንግስት ሀላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች በተገኙበት ተጀምሯል። በችግኝ ተከላው ላይ የተሳተፉትና አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡት የአካባቢው ነዋሪዎች በአካባቢው መራቆት ምክንያት ለተለያዩ ችግሮች ተጋልጠው መቆየታቸውን አስታውሰዋል። ከአካባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ ሀይሉ ጉልቲ በወንጪ ወረዳ የችግኝ ተከላ የተካሄደበት "ቱሉ ሶንቆሌ" ተራራ ከዓመታት በፊት በደን የተሸፈነ ነበር ብለዋል። ተራራው በጥቂት ዓመታት ውስጥ ተራቁቶ አፈሩም በጎርፍ እየተጠረገ ሲቸገሩ መቆየታቸውን ጠቅሰው፣ ባለፉት የበጋ ወራት ተራራውን መልሶ ለማልማት የጠረጴዛ እርከን ሲሰሩ መቆየታቸውን ተናግረዋል። በተራራውና በአካባቢው የገጠመውን የመሬት መራቆት መልሶ እንዲያገግም የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን እየተከሉ መሆናቸውንና ለተተከሉ ችግኞች የሚያደርጉትን እንክብካቤ እንደሚያጠናክሩ ተናግረዋል። አቶ ሽፈራው ጎቡ በበኩላቸው የተራቆተ መሬት ተመልሶ አረንጓዴ እንዲለብስ ችግኝ መትከል ብቻ በቂ ባለመሆኑ ሌሎች የአካባቢው ነዋሪዎችን ጭምር በማስተባበር ለተተከሉ ችግኞች እንክብካቤ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል። "ችግኝ መትከል ብቻውን በቂ ስላልሆነ የእንክብካቤ ሥራውም በቂ ትኩረትን ይሻል" ያሉት ደግሞ አቶ ወርቅነህ ታደሰ ናቸው። "ችግኝ ተክሎ መሄድ ብቻ ሳይሆን እንዲጸድቅ እያንዳንዱ ሰው ሀላፊነቱን መወጣት አለበት፤ የተተከሉ ችግኞች ሁሉ ለፍሬ እንዲበቁ የበኩላችንን እንወጣለን'' ሲሉም አከልዋል። አቶ ታደለ ድንቁ እና ወይዘሮ ወገኔ ድንቁም የሌሎቹን ሃሳብ የሚጋሩ ሲሆን በአካባቢያቸው የተተከሉ ችግኞች እንዲድቁም የሚጠበቅባቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል። ችግኝ የሚተከለው ለዛሬው ትውልድ ብቻ ሳይሆን ለመጪው ጭምር በመሆኑ የተተከለ ችግኝ ፍሬ እንዲያፈራ ሁሉም ሰው መንከባከብ አለበት ብለዋል።
የአረንጓዴ አሻራ ልማት የተራቆተ መሬታችን እንዲያገግም አድርጓል
Jul 2, 2025 56
ሀዋሳ ፤ሰኔ 25/2017 (ኢዜአ) ፡-ባለፉት ዓመታት በተከናወነ የአረንጓዴ አሻራ ልማት የተራቆተ መሬታቸው እንዲያገግም ማድረጉን በሲዳማ ክልል የዳራ ኦቲልቾ ወረዳ አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ የዳራ ኦቲልቾ ወረዳ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደገለጹት ባለፉት ተከታታይ ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ ልማት የተራቆተ አካባቢና የተጎዳ መሬታቸው አገግሟል፡፡ ይህም በጎርፍ የሚሸረሸረውን አፈር ማስቀረትና ለከብቶቻቸው የመኖ ሳር ማብቀል መጀመሩን ገልጸዋል፡፡ ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አርሶ አደር ማርቆስ ኬንካ፤ ለጎርፍ የተጋለጠ መሬታቸው ላይ እርከን በመስራትና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኞችን በመትከል ለም አፈር በጎርፍ እንዳይጠረግ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ ይህም የመሬቱን ለምነት በመጠበቁ ለከብቶቻቸው መኖ ማግኘታቸውንና አካባቢያቸውን ነፋሻ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡ ወይዘሮ አየለች ታደሰ በበኩላቸው የተጎዳ መሬታቸው በአረንጓዴ አሻራ ልማት እንዲያገግም በመደረጉ ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኞችን በመትከል ተጠቃሚ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር የተራቆተ መሬትን ስነ-ምህዳር በመቀየር ምንጮችና ጅረቶችን ዳግም እንዲፈልቁ ማድረጉን የገለጹት ደግሞ ሌላኛው አርሶ አደር አክሊሉ ጥላሁን ናቸው፡፡ እሳቸውም የአካባቢያቸውን ማህበረሰብ በማስተባበር የእርከን ስራ ላይ የአፈር ለምነት እንዲጠብቅና የተተከሉ ችግኞች እንዲጸድቁ ለተከታታይ ዓመት በሰሩት ስራ ለውጥ መመዝገቡን ተናግረዋል፡፡ የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው በክልሉ በሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ልማት ስራ የህብረተሰቡ ተሳትፎ እያደገ መጥቷል፡፡ በዚህም የተራቆቱ ቦታዎችን መልሶ ለማልማት በሚደረገው ጥረት ህብረተሰቡ በባለቤትነት እንዲሳተፍ በመደረጉ የጽድቀት መጠኑ ማደጉንም ገልጸዋል፡፡ የሲዳማ ክልል አረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር በተገኙበት በዳራ ኦቲልቾ ወረዳ በይፋ መጀመሩ ይታወሰል፡፡
ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተጀመሩ ተግባራትን ማጠናከር ያስፈልጋል
Jul 2, 2025 84
ቦንጋ ፤ ሰኔ 25/2017 (ኢዜአ)፡- ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተጀመሩ ተግባራትን ይበልጥ ማጠናከር እንደሚገባ ተገለጸ። "ጽዱ ኢትዮጵያን ባህል እናድርግ" በሚል መሪ ሃሳብ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) እና የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሚ በተገኙበት የፅዳት ዘመቻ በቦንጋ ከተማ ተጀምሯል። በማስጀመሪያው መረሃ ግብሩ ላይ ኢንጂነር ሌሊሴ ነሚ ባደረጉት ንግግር፤ የአካባቢን ንፁህና በመጠበቅ ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ማድረግ ይገባናል ብለዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል አባቶች ጠብቀው ያቆዩት ደን የአየር ብክለትን በማስወገድ ለኑሮ ተስማሚ ከባቢ እንዲፈጠር ምቹ መደላደል መሆኑን አንስተዋል። ከተሜነት እየተስፋፋ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ የሚከሰትን ብክለት ለማስወገድ የቆሻሻ አወጋገድ ላይ ጥንቃቄን በማድረግ ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ትኩረት መሰጠቱን ተናግረዋል። የአካባቢ ብክለትን ማስወገድና ፅዳትን ባህል ማድረግ ለጽዱ ኢትዮጵያ መሰረት መሆኑን ጠቁመዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት የተጀመረው የጽዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከተሞችን ለኑሮ ምቹ ለማድረግ አስቻይ ሁኔታን በመፍጠሩ ተግባሩን ባህል ማድረግ ይገባናል ያሉት ደግሞ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ናቸው። የፅዳት ዘመቻው አካባቢን ጽዱ ለማድረግ ፣ የቆሻሻ አወጋገድን ብቻ ሳይሆን ለአየር ብክለት ትኩረት በመስጠት ጤናን መጠበቅ የሚያስችል አቅምን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። የፅዱ ኢትዮጵያን ንቅናቄ ከአረንጓዴ አሻራ ጋር በማስተሳሰር ለምግብነት የሚውል ችግኝ መትከልና የሌማት ትሩፋት ስራዎችን ማጎልበትም እንዲሁ። ከንቅናቄው ተሳታፊዎች መካከል የቦንጋ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ፍርድነሽ ሀይሌ በሰጡት አስተያየት፤ የፅዳት ዘመቻው የአካባቢን ንፅህና ለመጠበቅ በጋራ የመስራትን ባህል ጎልብቶ እንዲቀጥል የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። አመራሮቹ ከፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ጎን ለጎን የአረንጓዴ አሻራቸውን ያኖሩ ሲሆን፤ የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎትንም አስጀምረዋል። በመረሃ ግብሩ ላይ የፌዴራል፣ የክልልና የዞን ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የአካባቢው ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
ችግኝ በመትከል የምናደርገውን ተሳትፎ እናጠናክራለን -ነዋሪዎች
Jul 2, 2025 56
መቱ፤ ሰኔ 25/2017 (ኢዜአ) ችግኝ መትከል የተጎዳ መሬት እንዲያገግምና ምርታማነት እንዲጨምር የሚያደርግ በመሆኑ ዘንድሮም በተከላው የሚያደርጉትን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩ የኢሉ አባቦር ዞን ነዋሪዎች ገለጹ። በኢሉባቦር ዞን የ2017 የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር ማስጀመሪያ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በዞኑ አሌ ወረዳ ተካሂዷል። በችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተሳተፉት አቶ ሲሳይ ወንድሙ፤ በየዓመቱ በተካሄዱ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሮች እየተሳተፉ መቆየታቸውን ገልጸዋል። ችግኝ መትከል የተጎዳ መሬት እንዲያገግም የሚያግዝና ምርታማነትን የሚጨምር በመሆኑ እንደ ባለፉት ዓመታት ሁሉ ዘንድሮም በተከላው በንቃት እንደሚሳተፉ ተናግረዋል። ሌላው በችግኝ ተከላው የተሳተፉት አቶ ሁሴን ከበደ በግልና በጋራ በሚከናወኑ የችግኝ ተከላዎች የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ጠቁመዋል። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ ልማት ስራዎች የአካባቢያቸው ገጽታ እየተለወጠ፣ ምርታማነትም እየተሻሻለ በመሆኑ ዘንድሮም ተሳትፏቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። የአሌ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ዮሐንስ ከበደ በበኩላቸው በወረዳው በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እንደ አቮካዶና ሙዝ ያሉ ፍራፍሬዎችን ጨምሮ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ላላቸው ችግኞች ትኩረት ተሰጥቶ ተከላው እንደሚከናወን ተናግረዋል። ችግኝ መትከል ተተኪ ትውልድን ታሳቢ ያደረገ በመሆኑ በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እንደሚተከሉ የገለጹት ደግሞ የኢሉ አባቦር ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ ናቸው። "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መሪ ሐሳብ በሚከናወነው የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በዞኑ ለተጎዱ መሬቶች ማገገምና ለኢኮኖሚያችን ማንሰራራት ጠቃሚ ለሆኑ ችግኞች ትኩረት ይሰጣል ብለዋል። በማስጀመሪያ መርሐግብሩ ላይ የተገኙት የኦሮሚያ ክልል ማረሚያ ቤቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ሻፊ ሁሴን፤ ችግኞችን መትከል የተፈጥሮ ሚዛን ለመጠበቅና የተጎዱ አካባቢዎች አገግመው ምርታማ አካባቢን ለመፍጠር እንደሚያግዝ ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት በዚህ መርሐግብር የተከናወኑ ተግባራት ለዚህ ማሳያ መሆናቸውን የጠቀሱት ኮሚሽነሩ፣ ብዙ የተጎዱ አካባቢዎች ዛሬ ላይ አገግመው ወደ አረንጓዴነት ተቀይረዋል ብለዋል። በዚህም የተራቆተ መሬት ለምነቱ እየተመለሰና ምርታማነቱ እየጨመረ መሆኑን ገልጸው፤ የደን ሽፋን መጠንም እየጨመረ መሆኑን ገልጸዋል። በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር ሕብረተሰቡ አካባቢውን ሊቀይሩ የሚችሉና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነቱን ሊያረጋግጡ የሚችሉ ችግኞችን የመትከልና የመንከባከብ ስራውን አጠናክሮ እንዲቀጥልም ኮሚሽነሩ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ባህር ዳር ከተማን ይበልጥ ፅዱና አረንጓዴ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው ቀጥለዋል
Jul 1, 2025 98
ባህርዳር ፤ ሰኔ 24/2017(ኢዜአ)፡- የባህር ዳር ከተማን ይበልጥ ፅዱና አረንጓዴ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት በሕብረተሰቡ የተቀናጀ ተሳትፎ ተጠናክረው መቀጠላቸውን የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ። "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መሪ ሃሳብ የባህር ዳር ከተማ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ ማስጀመረያ የንቅናቄ መረሃ-ግብር ዛሬ ተካሂዷል። የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው በመርሃ ግብሩ ላይ እንዳሉት ፤ ባህር ዳር ፅዱ ፣አረንጓዴና ደን የተጎናጸፈች ውብ ከተማ ናት። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብሮች የተተከለው ችግኝ የጽድቀት መጠንን በማሳደግ አበረታች ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን አውስተዋል። ከተማዋ በጣና ሀይቅና በዓባይ ወንዝ የተከበበች መሆኗን በመጠቀም በአረንጓዴ ልማት ለኑሮና ለቱሪስት የተመቸች ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ባህር ዳርን ይበልጥ ፅዱና አረንጓዴ ለማድረግ የሚያስችሉ ተግባራት በሕብረተሰቡ የተቀናጀ ተሳትፎ ተጠናክረው መቀጠላቸውን ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው ገልጸዋል። የከተማ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ የሰው ዘር ደመላሽ በበኩላቸው፤ በባህር ዳር በክረምቱ ከ492 ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ችግኝ ለመትከል ዝግጅት ተደርጎ ወደ ተግባር መገባቱን አስታውቀዋል። ከተዘጋጀው ችግኝ ውስጥም 45 በመቶ ለምግብነት የሚያገለግል አቡካዶ፣ ማንጎ፣ ሙዝ፣ ፓፓያና ሌላም የፍራፍሬ ችግኝ መሆኑን አመላክተዋል። የችግኝ ተከላውን ለማሳካትም ጉድጓድ መዘጋጀቱን ጠቁመው፤ ለተከላ ከተለየው መሬት ውስጥም ከ199 ሄክታሩ ካርታ ተሰርቶለታል ብለዋል። ከከተማው ነዋሪዎች መካከል አቶ ሙሉጌታ ዳኛው በሰጡት አስተያየት፤ ችግኝ ለማንም ተብሎ ሳይሆን ለራስና ለልጅ ልጅ የሚተርፍ ጥቅም ያለው መሆኑን በማመን ዛሬ መትከል መጀመራቸውን ተናግረዋል። የሚተከለውን ችግኝም ከአካባቢያቸው ማህበረሰብ ጋር በመሆን ተንከባክበው ለማሳደግ የድርሻቸውን እንደሚወጡም ገልጸዋል። የአረንጓዴ ልማት ላይ በራሳቸው ተነሳሽነት እየተሳተፉ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ወይዘሮ አበባ ሀይሉ ናቸው። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች፣ የግብርና ባለሙያዎችና የከተማዋ ነዋሪዎች በአዲስ ዓለም ሆስፒታል ግቢ ውስጥ ችግኝ በመትከል አሻራቸውን አኑረዋል።
የአረንጓዴ አሻራ ልማት ከተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ባለፈ የምግብ ዋስትና መሰረት ሆኖ እንዲዘልቅ እየተሰራ ነው
Jul 1, 2025 97
አምቦ፤ ሰኔ 24/2017 (ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተፈጥሮ ሃብት ልማት ባለፈ የምግብ ዋስትና መሰረት ሆኖ እንዲዘልቅ እየተሰራ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ ገለጹ። የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ፤ በምዕራብ ሸዋ ዞን አምቦ በመገኘት የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አስጀምረዋል። ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ቀደም ሲል ዝግጅት መደረጉን አንስተው ችግኞች ለተከላ ዝግጁ በመሆናቸው ሁሉም አሻራውን እንዲያኖር አስገንዝበዋል። በክልሉ ከዚህ በፊት የተተከሉ ችግኞች ለምተው ጥቅም በመስጠት ላይ መሆናቸውን አንስተው በቀጣይም ለደን ልማት፣ ለምግብነት የሚውሉ እና ለውበት የሚያገለግሉ ችግኞች የሚተከሉ መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም ለዚህ መርሃ ግብር መሳካት ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል አሻራውን ለማኖር የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርግ ጠይቀዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዲዳ ጉደታ፤ ለችግኝ ተከላው በተመረጡ አካባቢዎች ጎድጓዶች ተቆፍረው ዝግጁ መደረጋቸውን አንስተው ሁላችንም በመትከል አሻራችንን እናኑር ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል። በዞኑ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የምግብ ዋስትና እና ለደን ልማት የሚሆኑ ችግኞች መዘጋጀታቸውን አንስተዋል።
ትውልዱ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ ለሀገር በጎ አሻራውን ሊያኖር ይገባል - ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ
Jul 1, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/2017(ኢዜአ)፦ ትውልዱ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ ለሀገር በጎ አሻራውን ሊያኖር ይገባል ሲሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ-ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብጹዕ አቡነ ሳዊሮስ ገለጹ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ-ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ፣ የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ጃንጥራር አባይ፣ የቤተክርስቲያኗ አባቶች እና የከተማዋ አመራሮች ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አካባቢ የአረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በሀገርና በከተማ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመከላከል ለዜጎች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የማይተካ ሚና እየተጫወተ ነው። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያንም ከጥንት ጀምሮ በገዳማትና አድባራት ችግኞችን በመትከል ለመጠለያነት፣ ለደከማቸው ማረፊያና ለትውልድ ማስተማሪያነት እየተጠቀመች ነው ብለዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኞችን በመትከል የመንከባከብ ስራ ከቤተክርስቲያኗ ገዳማትና አድባራት ታሪክ ጋር ጥብቅ ትስስር ያለወ በጎ ተግባር መሆኑንም ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተሻለ ሀገር ግንባታ ጉልህ ሚና ያለው በመሆኑ ትውልዱ ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ በጎ ተግባርን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስና ከቤተ-ክርስቲያኗ አባቶች ጋር የአረንጓዴ አሻራችንን አሳርፈናል ብለዋል። አረንጓዴ አሻራ የሁሉም ዜጋ የጋራ የልማት አጀንዳ ነው ያሉት ምክትል ከንቲባው፥ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በመርሃ ግብሩ ችግኝ የመትከል ስራውን አጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል። የአዲስ አበባ የውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ኃላፊ ግርማ ሰይፉ በበኩላቸው በመዲናዋ 4 ነጥብ 2 ሚሊየን ችግኞችን መትከል የሚያስችል መርሃ ግብር በይፋ መጀመሩን አውስተዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ እና ብጹዓን አባቶች ያካሄዱት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብርም ለትውልዱ ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል። በቤተ-ክርስቲያኗ የፕሮጀክት መምሪያ ኃላፊ መላዕከ ህይወት ቆሞስ አባ ወልደየሱስ ሰይፉም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተጀመረው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ደህንነትን የመጠበቅ እና የበረከት ሥራ ነው ብለዋል። ቤተክርስቲያኗም በመርሃ ግብሩ ላይ የነቃ ተሳትፎ በማድረግ አርዓያነቷን እንደምታስቀጥል ጠቁመዋል። የቅኔና የመጽሐፍት ትርጓሜ መምህር ሊቀ-ጉባኤያት አባ ተክለሃይማኖት ወልዱ በበኩላቸው ችግኞችን መትከልና ተንከባክቦ ለፍሬ ማብቃት ከሁላችንም ይጠበቃል ነው ያሉት። ብፁዓን አባቶች በስፍራው ተገኝተው ያካሄዱት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሁሉም ዜጋ አርዓያ በመሆን ቀጣዩ ትውልድ የተሻለ ሀገር እንዲረከብ ለማድረግ ፋይዳ እንዳለውም ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የዘንድሮውን 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኞች የመትከል ሀገር አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ ልማት አካባቢ ማስጀመራቸው ይታወቃል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር የከተማዋን ገፅታ ቀይሯል - የአዳማ ከተማ ከንቲባ
Jul 1, 2025 120
አዳማ/ጅማ ፤ሰኔ 24/2017 (ኢዜአ)፡-የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር የከተማዋን ገፅታ መቀየሩን የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ገለጹ። በከተማዋ የአረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ዛሬ ተካሄዷል። የችግኝ ተከላ መርሐ ግብሩን ያስጀመሩት የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሀይሉ ጀልዴ እንዳሉት የተፈጥሮ ሃብት መመናመንን ለመከላከል የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ላይ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር በከተማ አስተዳደሩ የተተከሉ ችግኞች የከተማዋን ገፅታ ከመቀየር ባለፈ የገቢ ምንጭ በመሆን ጥቅም እያሰገኙ ነው ብለዋል። በዘንድሮ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም በ14 ተፋሰሶች ላይ 120 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ስፍራን ለማልማት ታቅዶ ዛሬ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ውስጥ መገባቱን ገልጸዋል። ከዚህም ባሻገር በትምህርትና በጤና ተቋማት እንዲሁም በወል መሬትና የኮሪደር ልማት በሚካሄድባቸውና በሌሎችም ስፍራዎች የችግኝ ተከላው በስፋት እንደሚካሄድ አውስተዋል። የአዳማ ከተማ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አለሙ ቂልጡ በበኩላቸው በከተማዋ ለፍራፍሬና ለዛፍ የሚውሉ ችግኞች እንደሚተከሉ ተናግረዋል። ለችግኝ ተከላው የቦታ መረጣና ጉድጓድ ዝግጅት ከማድረግ ባለፈ ህብረተሰቡ በበጎ ፈቃድ ለማሳተፍ ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን ተናግረዋል። በአዳማ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ላይ ችግኝ ሲተክሉ ያገኘናቸው አባገዳ መግራ ለገሰ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት በረሃማነትን ለመከላከል አረንጓዴ አሻራ ጉልህ ሚና መጫወቱን ተናግረዋል። የተራቆተ አካባቢን አረንጓዴ ለማልበስ የችግኝ ተከላው ወሳኝ በመሆኑ ችግኝ በመትከልና በመንከባከብ የዜግነት ግዴታቸውን እየተወጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። ሌላው የአዳማ ነዋሪ አቶ ግርማ ቶሌራ በበኩላቸው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የአካባቢያችንን ገጽታ ከመመለስ ባለፈ ለከተማዋ ውበት አሻራ የሚጥል ነው ብለዋል። በተመሳሳይም የጅማ ከተማ ከንቲባ አቶ ጣሃ ቀመር በዛሬው ዕለት በከተማዋ የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብርን አስጀምረዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩን ጥሪ በመቀበል የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ለተከታታይ ስድስት አመታት ችግኝ መተከሉን ጠቁመዋል። በክረምት ችግኝ ተከላ ፕሮግራሙ በ12 የችግኝ ጣቢያዎች ለምግብነት የሚውሉ ፍራፍሬዎችና እና ለዛፍ ጥላ የሚያገለግሉ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። በጅማ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ላይ ከተሳተፉት መካከል አቶ ነጂብ አለሙ በየዓመቱ በሚደረገው የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር መሳተፋቸውን ተናግረው መትከል ብቻም ሳይሆን መንከባከብ እንደሚገባም አመልክተዋል።