አካባቢ ጥበቃ
የውሃ አካል ዳርቻ አወሳሰን፣ ልማትና እንክብካቤ ረቂቅ አዋጅ ጸደቀ
May 22, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 14/2017(ኢዜአ)፦ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ አካል ዳርቻ አወሳሰን፣ ልማትና እንክብካቤ ረቂቅ አዋጅን በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። ምክር ቤቱ 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 31ኛ መደበኛ ስብሰባውን ዛሬ አካሂዷል።   በስብሰባው የውሃ አካል ዳርቻ አወሳሰን ልማትና እና እንክብካቤ ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ ውይይት አካሂዷል። በምክር ቤቱ የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና የአካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ(ዶ/ር) አዋጁን በተመለከተ ሪፖርትና የውሳኔ ሃሳብ አቅርበዋል።   ምክትል ሰብሳቢው እንዳሉት አዋጁ የውሃ አካላት ዳርቻ ርቀትን ለመወሰን፣ የውሃ አካላትን ከብክነት መጠበቅና ለሀገር ጥቅም በአግባቡ አገልግሎት ላይ እንዲውሉ ማድረግ ላይ ያተኮረ ነው። ከአረንጓዴ አሻራ፣ ገበታ ለትውልድ እና መሰል መርሃ ግብሮች የሚጣጣም ህግ ማውጣት ወሳኝ እርምጃ በመሆኑ አዋጁ መውጣቱን አብራርተዋል። የውሃ አካላትን የማልማት እና የመንከባከብ ስራው ውጤታማ እንዲሆን አዋጁ አዎንታዊ ሚና እንደሚጫወትም አስረድተዋል። አዋጁ የውሃ አካላት ጥበቃና እንክብካቤን በማሻሻል በርካታ ውጤቶችን ይዞ የሚመጣ ትልቅ እርምጃ ነው ብለዋል። የውሃ አካላት ዳርቻ ወሰን እንዲሁም በውሃ አካላት ብክለት የህግ ጥሰቶች ሰፈጸሙ እርምጃ የሚወሰድበትን አግባብ መደንገጉንም አብራርተዋል። ነባር ሆኑ ወደ ስራ የሚገቡ አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች የሚለቁት ፍሳሽ በውሃ አካላት ላይ ጉዳት እንዳያደርሱ ትኩረት መስጠቱንም አስረድተዋል። ምክር ቤቱ በአዋጁ ዙሪያ የቀረበለት ሪፖርትና የውሳኔ ሃሳብ ላይ ተወያይቶ በሙሉ ድምፅ አጽድቋል።
በክልሉ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ83 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚሸፍኑ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል
May 21, 2025 85
አርባምንጭ፤ግንቦት 13/2017 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ83 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚሸፍኑ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት መደረጉን የደን፣አካባቢ ጥበቃና ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ አቶ ግዛቴ ግጄ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፥ በክልሉ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 83 ሺህ 395 ሄክታር መሬት የሚሸፍኑ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል። ችግኞቹ በክልሉ በ12 ዞኖች በመንግስት፣በግለሰብ፣ በማህበራትና መንግስታዊ ባልሆኑ ተቋማት በ1 ሺህ 495 የችግኝ ጣቢያዎች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። የተዘጋጁት ችግኞች ለአካባቢ ጥበቃ ጨምሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው መሆናቸውን አመልክተዋል። አሁን ላይ ተከላውን ለማሳካት የሚያግዙ የጉድጓድ ቁፋሮና ሌሎች የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል። የአረንጓዴ አሻራ ልማት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እያስገኘ መሆኑን ያነሱት አቶ ግዛቴ፥ የአየር ሚዛንን ከማስተካከል ባለፈ የአፈር ለምነትና የውሃ መጠንን በመጨመር ምርትና ምርታማነት እንዲረጋገጥ እያስቻለ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የሚደረገውን ጥረት ከማገዝ አልፎ ለኢኮ ቱሪዝም መነቃቃት ልዩ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰዋል። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በ2011 ዓ/ም የደን ሽፋኑ 17 በመቶ የነበረ ሲሆን በተደረገው ተከታታይ የአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄ የደን ሽፋኑ ወደ 23 ነጥብ 17 በመቶ ማደጉን ከቢሮው የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በክረምት የጎርፍ ተጋላጭነትን ለመቀነስ የሚያስችሉ ተግባራት አከናውነናል -አርሶ አደሮች
May 21, 2025 94
ሰቆጣ ፤ግንቦት 13/2017 (ኢዜአ) ፡- በክረምት የጎርፍ ተጋላጭነትን ለመቀነስ የሚያስችሉ ተግባራትን ከወዲሁ ማከናወናቸውን በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር የጋዝጊብላና ደሃና ወረዳዎች አርሶ አደሮች ገለጹ። በመጪው ክረምትም ሊከሰት የሚችል ጎርፍ ለመከላከል ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች 28 ሺህ በላይ ሰዎችን በማሳተፍ በተራራና በእርሻ መሬት ላይ የእርከን ስራዎች ማከናወን መቻሉን የብሔረሰብ አስተዳደሩ አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ጽህፈት ቤት አመልክቷል።   በብሔረሰብ አስተዳደሩ ጋዝጊብላ ወረዳ የዲውና ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ገናን በዓካል ፤ ባለፈው ክረምት በተከሰተ የጎርፍና መሬት መንሸራተት መኖሪያ ቤታቸውና የእርሻ መሬታቸው ላይ ጉዳት እንዳደረሰባቸው አስታውሰዋል ። በዘንድሮ ክረምት ተመሳሳይ ክስተት እንዳያጋጥማቸው በበጋው ወቅት ከአካባቢው አርሶ አደሮች ጋር በመሆን የጎርፍ ማፋሰሻና የተጠናከረ የተራራ ላይ እርከን መስራታቸውን ተናግረዋል። በደሃና ወረዳ ብርብራ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ማሞ ፀጋው በበኩላቸው "ባለፈው ክረምት በአካባቢው ያጋጠመው የጎርፍና መሬት መንሸራተት አደጋ ዘንድሮ እንዳይደገም ህብረተሰቡን ያሳተፈ የእርከን ስራ ሰርተናል" ብለዋል። "አካባቢያችን ተራራማ በመሆኑ በክረምቱ በመኖሪያ ቤታችንም ሆነ በእርሻችን ላይ ሊከሰት የሚችል የጎርፍ አደጋ ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራትን በበጋው ወቅት አከናውነናል " ያሉት አርሶ አደር ማሞ የተራራ ላይና የእርሻ ውስጥ የእርከን ስራ ማከናወናቸውን ጠቅሰዋል። ያከናወኑት የእርከን፣ የውሃ ማፋሰሻ ቦይ ግንባታና ሌሎች ስራዎች ጎርፍና የመሬት መንሸራተት ከሚያደርስባቸው የቁስና የተዘራ ሰብል ውድመት እንደሚታደጋቸው አርሶ አደሮቹ ተናግረዋል።   በዋግ ኽምራ ብሄረሰብ አስተዳደር አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ፅህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ምህረት መላኩ እንደገለፁት ባለፈው ክረምት በሶስት ወረዳዎች ላይ ባጋጠመው የጎርፍና መሬት መንሸራተት 45 ሽህ ሄክታር መሬት የሸፈነ ሰብል ላይ ጉዳት ደርሷል። በዚህም በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጎጂ መሆናቸውን አስታውሰው ችግሩ በመጭው ክረምትም እንዳይከሰት ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች 28 ሽህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በተራራና በእርሻ መሬት ላይ የእርከን ስራዎች መከናወኑን ተናግረዋል። "በክረምት ወራት የሚያጋጥሙ አደጋዎችን መቀነስ የሚያስችል በበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች ተከናውኗል" ያሉት ደግሞ የብሄረሰብ አስተዳደሩ ግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ ናቸው።   የጎርፍና የመሬት መንሸራተት ተጋላጭነትን ለመቀነስ በተሰሩ የእርከን ስራዎች በክረምት ወራት በስነ- ህይወታዊ ዘዴ የመሸፈን ተግባራት ለማከናወን ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል።  
ኢትዮጵያ ለኢጋድ አባል አገራት አስተማማኝ እና ወቅታዊ የሜቲዎሮሎጂ መረጃዎችን ለማጋራት ዝግጁ ናት -ሚኒስትር ኢንጅነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር)
May 21, 2025 94
አዲስ አበባ ፤ግንቦት 13/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ለምስራቅ አፍሪካ የልማት በየነ መንግስታት አባል አገራት አስተማማኝ እና ወቅታዊ የሜቲዎሮሎጂ መረጃዎችን ለማጋራት ዝግጁ መሆኗን የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጅነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ሚኒስትር ኢንጅነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) ከኢጋድ የስራ ሃላፊዎችና ከኢጋድ አባል አገራት የውሃ ሚኒስቴር ተወካዮች ጋር በተለያዩ የዘርፉ ጉዳች ዙሪያ ውይይት አድርገዋል።   በዚሁ ወቅትም በኢጋድ አባል አገራት ድርቅ፣ ጎርፍ እና አውሎ ነፋስ ተደጋግመው የሚከሰቱ የተፈጥሮ አደጋዎች ናቸው ብለዋል። በነዚህ እና መሰል የተፈጥሮ አደጋዎች ምክንያትም በሰው፣ በእንስሳት እና በንብረት ላይ ጉዳቶች እንደሚከሰቱ አንስተዋል። ዛሬ የተደረገው ውይይትም በአባል አገራቱ መካከል የተደራጀ እና የተቀናጀ የሜቲዎሮሎጂ መረጃዎችን በመለዋወጥ በተፈጥሮ አደጋዎች የሚከሰቱ ጉዳቶችን ለማስቀረት ያለመ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የተፈጥሮ አደጋዎችን ቀድሞ ለመከላከል የተተነተነ እና የተደራጀ የሜቲዎሮሎጂ መረጃዎች እንደሚያስፈልጉ ጠቁመው፤ ይህን ለማድረግም የአገራት ትብብር እንደሚያስፈልግ ነው የጠቀሱት፡፡ ይህን ትብብር እውን ለማድረግ በአባል አገራቱ መካከል የተደረገው ምክክር አስቻይ ሁኔታ እንደሚፈጥር ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ ካሏት የሜቲዎሮሎጂ ጣቢያዎች መካከል 60 በመቶው የሚሆኑት ዘመናዊ ማሽን የተገጠመላቸው መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በዘርፉ ያላትን ትልቅ አቅም ለቀጣናው አገራት እያጋራች እንደምትገኝ ገልጸው፣ በቀጣይም አስተማማኝ የሜቲዎሮሎጂ መረጃዎችን ለጎረቤት አገራት ተደራሽ ለማድረግ ዝግጁ መሆኗን አረጋግጠዋል፡፡   በኢጋድ የአየር ንብረት ትንበያና ትግበራ ማዕከል ኃላፊ አብዲ ፊዳ በበኩላቸው፣ ለአባል አገራቱ የሜትሮሎጂ መረጃዎችን መለዋወጥ አደጋዎችን ቀድሞ ለመከላከል የጎላ ሚና አለው ብለዋል፡፡ ለዚህ የመረጃ ልውውጥ ኢጋድ የበኩሉን ሚና እንደሚወጣ ተናግረው፤ የኢትዮጵያን የሜቲዎሮሎጂ መረጃ አያያዝን ምርጥ ተሞክሮ ወደ ሌሎች አገራት ለማስፋት እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡        
የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን መሰረት ያደረገ የሰው ሀብት ልማት የኢትዮጵያን ዘላቂ ዕድገት ለማረጋገጥ ወሳኝ ነው
May 20, 2025 78
አዲስ አበባ፤ግንቦት 12/2017(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን መሰረት ያደረገ የሰው ሀብት ልማት የኢትዮጵያን ዘላቂ ዕድገት ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለፁ። ከሰሃራ በታች ያሉ የአፍሪካ ሀገራት የኢራስመስ ፕላስ 2025 ጉባኤ "የትምህርት ሚና ለአረንጓዴ ልማት ሽግግር" በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እየተካሄደ ይገኛል። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን በተለያዩ የልማት ኢኒሼቲቮች አካታ እየሰራች ትገኛለች። የታዳሽ ሃይል ልማትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን ዘላቂ የዕድገት ጉዞ ቁርጠኝነት የሚያሳዩ ናቸው ያሉት ሚኒስትሯ፥ ከንግግር ባለፈ በተግባር ስኬታማ ስራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ሂደትም ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል እየተፈጠረ መሆኑን ጠቅሰው፥ የሰው ሀብት ልማት ስራዎችም በዚሁ አቅጣጫ እየተተገበረ ይገኛል ነው ያሉት። በሀገሪቱ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ መሰረት የተቃኘና በክህሎትና በእውቀት የዳበረ የሰው ሀብተ ልማት የኢትዮጵያን ዘላቂ ዕድገት ለማረጋገጥና የተወዳዳሪነት አቅምን ለማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ለአፍሪካ ጭምር አቅም የሚሆን ተግባር እያከናወነች ነው ያሉት ሚኒስትሯ፥ ይህም ሀገራዊና አህጉራዊ የመጪ ዘመን ርዕይን ለማሳካት ጉልህ ሚና እንዳለው ጠቅሰዋል። የአውሮፓ ሀገራት በኢራስመስ መርሃግብር በኩል ኢትዮጵያን ጨምሮ ከአፍሪካ ሀገራት ጋር በአቅም ግንባታና በስልጠና ዘርፍ በትብብር እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰው፥ ይህም ለሰው ሀብት ልማት አጋዥ አቅም ይፈጥራል ብለዋል። በኢትዮጵያ የአውሮፓ ህብረት ተወካይ ሮቤርቶ ሺሌሮ በበኩላቸው፥ የአውሮፓ ህብረት ለትምህርት ዘርፍ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን አንስተዋል። ጉባኤውም በአውሮፓና አፍሪካ አገራት መካከል ያለውን ትብብር ለማጠናከር እንደሚያስችል ተናግረዋል። በትምህርት ሚኒስቴር የከፍተኛ ትምህርት አካዳሚክ ጉዳዮች መሪ ስራ አስፈጻሚ ኤባ ሚጀና(ዶ/ር) የአውሮፓ ህብረት በኢራስመስ መርሃ ግብር በኩል ከአፍሪካ አገራት ጋር በትብብር እየሰራ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ሀገራት ነፃ የትምህርት እድል፣ በትብብር ምርምር መስራትና ሌሎች የፕሮጀክት ድጋፎች እያገኙ መሆናቸውንም ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ምርምር ምክትል ፕሬዝዳንት ጄይሉ ዑመር (ዶ/ር) የኢራስመስ መርሃግብር ከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ለማጠናከር አስተዋፅኦ እንዳለው ገልጸዋል።
የኢጋድ አባል ሀገራት አስተማማኝ የአየር ንብረት መረጃን ለማመንጨት ጠንካራ ስርዓት መዘርጋት አለባቸው
May 19, 2025 130
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2017(ኢዜአ)፦ የኢጋድ አባል ሀገራት አስተማማኝ የአየር ንብረት መረጃን ማመንጨት የሚያስችል ስርዓት ለመዘርጋት የሚያደርጉትን ጥረት ማጠናከር እንደሚገባቸው የውኃና ኢነርጂ ሚኒስትር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር ኢ/ር) ገለጹ። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) የአየር ጠባይ ትንበያና ትግበራ ማዕከል ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር 70ኛው የአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ምልከታ መድረክ እያካሄደ ይገኛል። የውኃና ኢነርጂ ሚኒስትር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር ኢ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት በአፍሪካ ቀንድ በተደጋጋሚ የሚከሰተው ድርቅና ጎርፍ በርካቶችን እየፈተነ ነው።   ግብርና፣ የምግብ ሉዓላዊነት፣ የውሃ ሀብት፣ ቱሪዝምና ጤና በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ከሚደርስባቸው ዘርፎች በዋናነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን አንስተዋል። በኢትዮጵያ አስተማማኝና ትክክለኛ የአየር ትንበያ መረጃን መተንተንና ማሰራጨት የሚያስችል የተቋም ማዘመንና ጠንካራ ስርዓት ለመዘርጋት እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። የኢጋድ የአየር ጠባይ ትንበያና ትግበራ ማዕከል ወቅታዊና አስተማማኝ የአየር ጠባይ መረጃ በማቅረብ የአባል ሀገራቱ የዘርፉን ባለሙያዎች አቅም ለማጎልበት የሚሰራው ስራ የሚደነቅ መሆኑንም ተናግረዋል። በየሀገራቱና በአጠቃላይ በቀጣናው በእውቀት ላይ የተመሰረተ ትክክለኛና አስተማማኝ የአየር ንብረት መረጃን ማመንጨት የሚያስችሉ ስርዓቶችን ለመዘርጋት ኢንቨስት ማድረግ አለብን ነው ያሉት።   የኢጋድ ምክትል ዋና ጸሐፊ መሀመድ አብዲ ዋሬ በበኩላቸው በአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ለውጥ የተለያዩ አደጋዎችና ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት ላይ ተፅዕኖ እያሳደረ ይገኛል ብለዋል። ኢጋድ በአየር ጠባይ ትንበያና ትግበራ ማዕከል በኩል ለቀጣናው የአየር ንብረት ትንበያ መረጃን ተደራሽ እያደረገ እንዲሁም ለሀገራቱ ድጋፍ እየሰጠ እንደሆነም ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ፥ መንግስት ኢንስቲትዩቱንና የክልል የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ማዕከላትን እያጠናከረ መሆኑን ገልጸዋል። የሙያተኞችን አቅም ለማሳደግና ዘመናዊ የሚቲዎሮሎጂ ምልከታ ስርዓት ለመዘርጋት እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።   ከመጪው ሰኔ እስከ መስከረም ባለው ወቅት ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ እንደሚጠበቅ የትንበያ መረጃዎች እንደሚያሳዩ የተናገሩት የኢጋድ የአየር ንብረት ትንበያና ትግበራ ማዕከል የአየር ንብረት ለውጥ ተመራማሪ ትጥቄ ካሳ(ዶ/ር) ናቸው። በክረምቱ ወቅት ከመደበኛ በላይ የሚጠበቀው ዝናብ ለግብርና እንቅስቃሴ አስፈላጊ በመሆኑ መንግስታት ከሚመለከታቸው ባለሙያዎች ጋር በመነጋገር አስፈላጊውን ዝግጅት ማድረግ እንደሚጠበቅባቸውም አስገንዝበዋል። የዝናቡ ሁኔታ የጎርፍና መሰል አደጋዎችን እንዳያስከትልም መረጃን በማጠናከር ቅድመ ጥንቅቄ ማድረግ ይገባልም ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ ሀገር በቀል የብዝኃ ህይወት ሀብቶቿን ጠብቃ ለትውልድ ለማስተላለፍ እየሰራች ነው - የብዝኃ ህይወት ኢንስቲትዩት
May 19, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ሀገር በቀል የብዝኃ ሕይወት ሀብቶቿን ጠብቃ ለትውልድ ማስተላለፍ የሚያስችሉ አሰራሮችን እየተገበረች እንደምትገኝ የብዝሃ ህይወት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ካርታ ካስኬ(ዶ/ር) ገለጹ። ዓለም አቀፍ የብዝሀ ሕይወት ቀን ለ24ኛ ጊዜ “ከተፈጥሮ ጋር መስማማት ለዘላቂ ልማት” በሚል መሪ ሀሳብ ከግንቦት 12 እስከ 16 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይከበራል። የኢትዮጵያ ብዝኃ ህይወት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ካርታ ካስኬ(ዶ/ር) በሰጡት መግለጫ ብዝኃ ህይወት ለስነ ምህዳር ሚዛን መጠበቅ፣ ለምግብ ስርዓት ዘላቂነት እና ለሰው ልጆች ደህንነት ከፍተኛ ሚና አለው ብለዋል። አዲሱ የግብርና እና ገጠር ልማት ፖሊሲ የብዝኃ ህይወት ጥበቃና አጠቃቀምን በማጎልበት ሀገር በቀል ዝርያዎች እንዳይጠፉ መጠበቅ የሚያስችል አሰራር መዘርጋት እንደሚገባ አቅጣጫ መቀመጡን ተናግረዋል። ከዚህ አንጻር ኢትዮጵያ የብዝኃ ህይወት ሃብቶቿን ጥበቃ እያጎለበተች መሆኑን ጠቁመው ሀገር በቀል ዝርያዎች እንዳይጠፉ የሚያስችል ሥርዓት ተግባራዊ እያደረገች መሆኗም አንስተዋል፡፡ በብዝኃ ህይወት ያላት ዕምቅ ሃብት መጠበቅና ለቀጣይ ትውልድ ማስተላለፍ የሁሉም ድርሻ ርብርብ እንደሚጠይቅ ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። የዘንድሮው የብዝኃ ህይወት ቀን የዘርፉን ሀብት ጥበቃ ማጎልበት በሚያስችሉ የፓናል ውይይቶች፣ አውደ ርዕይ፣ የመስክ ጉብኝትና ሀገር በቀል ችግኞችን በመትከል ይከበራል ብለዋል። የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አብዮት ብርሃኑ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የብዝሀ ህይወት ስምምነት ፈርመው ከተቀበሉ 196 ሀገራት መካከል አንዷ መሆኗን ገልጸዋል፡፡ ስምምነቱ የፀደቀበትን ዕለት ለማስታወስ ሲባል ግንቦት 14 ዓለም አቀፍ የብዝኃ ሕይወት ቀን ተብሎ መወሰኑን ጠቁመው፤ ይህም በዓለም አቀፍ ደረጃ እ.እ.አ ከ2002 ጀምሮ በየዓመቱ በድምቀት እየተገበረ ይገኛል ብለዋል፡፡
በጋምቤላ ከተማ ከ14 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ ደረቅ ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያስችል ፕሮጀክት ይፋ ተደረገ
May 19, 2025 111
ጋምቤላ፤ ግንቦት 11/2017(ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ከተማ ከ14 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ ደረቅ ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያስችል ፕሮጀክት ዛሬ ይፋ ተደርጓል። በከተማው የአካባቢ ብክለትን ለመከላከልና ደረቅ ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል ለሚደረገው ጥረት የአጋር አካላት ተሳትፎ ሊጠናከር እንደሚገባም ተጠቁሟል። የጋምቤላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሳይመን ሙን (ዶ/ር) በፕሮጀክቱ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ ተገኝተው እንዳሉት መንግስት የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል የሚያስችሉ ፖሊሲዎችን ቀርፆ ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል።   በተለይም ደረቅ ቆሻሻን በመሰብሰብና መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል የተጀመሩ ስራዎች ለወጣቱ የስራ እድል በመፍጠር ረገድም አዎንታዊ ሚና እንዳላቸው ተናግረዋል። ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ይፋ የተደረገው ፕሮጀክትም ያገለገሉ ፕላስቲኮችና ደረቅ ቆሻሻዎችን መልሶ ጥቅም ላይ ከማዋል ባለፈ የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። የፕላስቲክ ቆሻሻ ለረጅም ዓመታት ሳይበሰብስ በመቆየት አፈርን በኬሚካል የመበከል አቅም ያለው መሆኑን ጠቅሰው ፕሮጀክቱ በጋምቤላ ከተማ ተግባራዊ መደረጉ ችግሩን የሚያቃልል ነው ብለዋል። ማህበረሰቡም የፕላስቲክ ምርቶችን ተጠቅሞ ሲያስወግድ አካባቢን በማይበክል መልኩ ሊሆን እንደሚገባ ጠቅሰው የከተማ አስተዳደሩም ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ተናግረዋል ። ፕሮጀክቱ ደረቅና የፕላስቲክ ቆሻሻዎችን ሰብስቦ መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል ይሰራል ያሉት ደግሞ የኖርዌይ ቤተክርስቲያን እርዳታ ድርጅት የጋምቤላ ክልል አስተባባሪ አቶ በቃሉ ዳኜ ናቸው።   ከ14 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ለሁለት ዓመታት የሚተገበረው ይህ ፕሮጀክት በአካባቢ ማስዋብና በቆሻሻ ማስወገድ ላይ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ ማህበራትና ወጣቶችን በማቀፍ የሚተገበር መሆኑን አስረድተዋል። በፕሮጀክቱ ይፋዊ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ ከወዳደቁ የፕላስቲክ ቆሻሻዎች ለተለያዩ አገልግሎቶች የሚውሉ የፈጠራ ስራዎችም ቀርበዋል።  
በዞኑ በተፋሰስ ልማት ባገገሙ አካባቢዎች ባከናወነው የልማት ስራ ተጠቃሚ ሆነናል - አርሶ አደሮች
May 18, 2025 119
ወልቂጤ፤ ግንቦት 10/2017 (ኢዜአ) ፡-በጉራጌ ዞን በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መልሰው እንዲያገግሙ በተደረጉ አካባቢዎች እያከናወኑ ባሉት የልማት ስራ ተጠቃሚ መሆናቸውን የዞኑ አርሶ አደሮች ገለፁ። በዞኑ የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት ስራ በተከናወነባቸው አካባቢዎች የለማ ከ75 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በሰብልና በፍራፍሬ እየተሸፈነ መሆኑን ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታውቋል። አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው መልሰው እንዲያገግሙ በተደረጉ አካባቢዎች እያከናወኑ ባሉት የልማት ስራ ተጠቃሚ ሆነዋል። በተፋሰስ ልማቱ በለሙ አካባቢዎች ድንች በመትከል ተጠቃሚ ከሆኑ አርሶ አደሮች መካከል በወረዳው የአምበሊ ቀበሌ ነዋሪው መልስ ሟነንዳ ስራው የአፈር ለምነት እንዲመለስ በማድረጉ ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ገልጸዋል።   ከዚህ ቀደም ትኩረት ባለመስጠታቸው ለጉዳት ተጋልጦ የነበረው አካባቢ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በተሰራ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ አገግሞ ዘርፈ ብዙ ጥቅም እየሰጠን ይገኛል ብለዋል። ሌላኛዋ አርሶ አደር ዘምዘም አህመዲን በቀበሌው ከዚህ ቀደም በተከናወነ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የተጎዱ መሬቶች እያገገሙ መሆኑንና አፈር እንዳይሸረሸር ማድረጉን ተናግረዋል። ለምነቱ በተመለሰው ቦታ ላይም የተለያዩ ሰብሎችና የመኖ ተክሎችን በማልማት የበለጠ ተጠቃሚ መሆናቸውን አመልክተዋል። ለምነቱ በተመለሰው መሬት ላይ እንሰትና ድንች በመትከል በተፋሰስ በለማው መሬት ላይ ደግሞ የገብስ ምርጥ ዘር ለመዝራት መዘጋጀታቸውን የገለፁት ደግሞ በወረዳው የኰኴራ ቀበሌ አርሶ አደር አቶ ዘራብዛ ግርማ ናቸው። በአሁኑ ወቅትም የቤተሰብ ቀለብ በአግባቡ ከመቻል አልፈው ለገበያ ጭምር ለማምረት እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። የጉራጌ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ እና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ ለኢዜአ እንዳሉት፣ በዞኑ በተከናወኑ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የለሙ አካባቢዎች ሙሉ ለሙሉ በሰብልና ፍራፍሬ ተክሎች እየተሸፈኑ ነው።   አካባቢዎቹ ከዚህ ቀደም ገላጣና ለም አፈራቸው ተሸርሽረው ከአገልግሎት ውጪ ሆነው የቆዩ ቢሆንም በማህበረሰብ ተሳትፎ በተከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ አገግመው በሰብሎችና ፍራፍሬዎች መሸፈናቸውን አመልክተዋል። በዚህም በዞኑ በተፋሰስ ስራ የለማ ከ75 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በተለያዩ የሰብል አይነቶችና ፍራፍሬዎች ከመሸፈናቸውም በላይ ለመኖና ለንብ እርባታ ልማት እንዲውሉ መደረጉን ተናግረዋል። በወረዳቸው የአፈር ለምነትን የሚጨምሩ የእርከን ስራዎች፣ ውሃ የማቀብና የመከለል ስራ በማከናወን ከ13 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በድንች፣ በፍራፍሬና በቅመማ ቅመም መሸፈኑን የተናገሩት ደግሞ የእዣ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መቻል ተሰማ ናቸው።   በተጨማሪም የንብ እርባታ እና የተለያዩ የመኖ ሰብሎች እየለሙ መሆኑን አክለው 34 ሺህ የሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችም በዚሁ ልማት አዳዲስ የስራ እድሎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉንም አስረድተዋል።        
የስነ-ምድር አፈጣጠርን የሚያሳዩ አካባቢዎችን በመንከባከብ እና በመጠበቅ ለኢኮኖሚ ጠቀሜታ ማዋል ይገባል
May 18, 2025 118
አዲስ አበባ፤ግንቦት 10/2017(ኢዜአ)፡-ህብረተሰቡ የስነ-ምድር አፈጣጠርን የሚያሳዩ አካባቢዎችን በመንከባከብ እና በመጠበቅ ለኢኮኖሚ ጠቀሜታ ማዋል እንደሚገባ በአዲስ አበባ እና ቦትስዋና ዩኒቨርሲቲዎች የስነ-ምድር መምህር አስፋውወሰን አስራት (ፕ/ር) ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ውስጥ በዪኔስኮ ብዝሃ ሃብት ካስመዘገቡት ሀገራት አንዷ ስትሆን በርካታ የሚዳሰሱ፣ የማይዳሰሱ እና ጥብቅ ባዪስፌር ሀብቶች በዩኔስኮ እውቅና ተሰጥቷቸው የተመዘገቡ ናቸው። መንግስት ከለውጡ ወዲህ ለቱሪዝም ዘርፉ በሰጠው ትኩረት ከኢኮኖሚ ምሰሶ መካከል አንዱ እንዲሆን ያደረገ ሲሆን አዲሱ ረቂቅ የቱሪዝም ፖሊሲ የጂኦቅርስ ቦታዎችን መጠበቅ፣ ጂኦፓርኮችን ማቋቋም እና ለጂኦቱሪዝም አስፈላጊነት ትኩረት ሰጥቷል። በዚህም ኢትዮጵያ በጂኦቱሪዝም በርካታ ሃብቶች ያላት ሀገር ስትሆን የሶፈኡመር ዋሻ፣ ገርአልታ፣ ኮንሶ፣ አፋር፣ ባሌ ተራሮችና የሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርኮች ተጠቃሽ ናቸው።   በአዲስ አበባ እና ቦትስዋና ዩኒቨርሲቲዎች የስነምድር መምህር አስፋውወሰን አስራት (ፕ/ር) በኢትዮጵያና በአጠቃላይ ምስራቅ አፍሪካ ለስነ-ምድር አፈጣጠር ምርምር የሚሆኑ በርካታ ስፍራዎች ያሉባቸው መሆኑን ገልጸዋል። እነዚህ የላቀ ሁለንተናዊ እሴት ያላቸው ስፍራዎች በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስ እና የባህል ድርጅት /ዩኔስኮ/ በጂኦፓርከነት ተመዝግበው ጥበቃ እንደሚደረግላቸው ጠቁመዋል። እስካሁን 229 ጂኦፓርኮች ጥበቃ እየተደረገላቸው መሆኑን ጠቁመው፥ በአፍሪካ የተመዘገቡት ሁለት ብቻ ሲሆኑ እነሱም ታንዛኒያ እና ሞሮኮ መሆናቸውን አንስተዋል። በተለይም በኢትዮጵያ የስምጥ ሸለቆ አፈጣጠርን በአጭር ቦታ የሚያሳዩ የተፈጥሮ አቀማመጦች መኖራቸውን አንስተው፤ ስፍራዎቹ የዓለም ቅርስ መሆን የሚችሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። ህብረተሰቡ እነዚህን የስነ-ምድር አፈጣጠርን የሚያሳዩ አካባቢዎችን በመንከባከብ እና በመጠበቅ ለኢኮኖሚ ጠቀሜታ ማዋል እንደሚገባውም ጠቁመዋል።   በኢትዮጵያ ተገልጠው የሚታዩ ተራራዎች የሚያመለክቱት በርካታ ታሪክ መኖሩን ነው ያሉት ፕሮፌሰሩ፥ ኢትዮጵያ ለዚህ ዘርፍ እምቅ ጸጋ ያላት ሀገር መሆኗንም ጠቁመዋል፡፡ በጂኦፓርኮች እና ጂኦቱሪዝም ለዘላቂ ልማት እና ፋይዳዎች ላይ ግንዛቤ ለመፍጠር ቀጣናዊ ወርክሾፕ በአዲስ አበባ መካሄዱ ይታወሳል። የስልጠናው ተሳታፊ የተለያዩ ሀገራት ተወካዮች በኦሮሚያና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች ውስጥ የሚገኙ የተመረጡ የጂኦሎጂ እና የአርኪኦሎጂ ቦታዎች ላይ የመስክ ጉብኝት ማድረጋቸውም እንዲሁ።
በክልሉ እየተከናወነ ያለው የተፋሰስ ልማት የአፈር መሸርሸረን ከመከላከል ባለፈ ለምርታማነት መጨመር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
May 14, 2025 224
አሶሳ፤ ግንቦት 6/2017(ኢዜአ):- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እየተከናወነ ያለው የተፋሰስ ልማት የአፈር መሸርሸረን ከመከላከል ባለፈ ለምርታማነት መጨመር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አርሶ አደሮች ተናገሩ። የግብርና ባለሙያዎች በበኩላቸው በክልሉ የተፋሰስ ልማትን በማጠናከር የህዳሴ ግድብ በደለል እንዳይሞላ አስተዋጽኦ ለማበርከት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የተከናወነውን የተፋሰስ ልማትና የተገኘውን ውጤት በተመለከተ ኢዜአ በክለሉ የተለያዩ አካባቢዎች ምልከታ ያደረገ ሲሆን አርሶ አደሮችና የግብርና ባለሙያዎችና አመራሮችን አነጋግሯል። የተፋሰስ ልማት ሥራ የጠፉ ምንጮችን ከመመለስና የአካባቢን ሥነ ምህዳር ከመለወጥ ጎን ለጎን ለተቀናጀ የግብርና ሥራና ምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ ማድረጉን አርሶ አደሮች ይናገራሉ። በክልሉ ኡራ ወረዳ ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት አርሶ አደር ሀዋ መሀመድ በክልሉ የተለያዩ ወረዳዎች ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ስራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ተገኝተዋል ብለዋል። ሌላኛው አርሶ አደር አማረ አሰፋ፤ በተፋሰስ ልማቱ የአፈር ለምነትን በመጠበቅና ምርታማነትን ከማሳደግ ባለፈ አካባቢው በደን በመሸፈኑ ከቀርከሃና ሌሎች ችግኞች ለሽያጭና ለተለያዩ አገልግሎቶች እያዋልን ነው ብለዋል።   በተሰራው የተፋሰስ ልማት አካባቢው ከእንስሳት እንዲጠበቅ በማድረግ የተተከሉ የቀርቀሃ እና ሌሎች ችግኞችም አሁን ላይ ለሽያጭ ደርሰው ገቢ እያስገኙ ነው ሲሉ ተናግረዋል። በክልሉ የአቡራሞ ወረዳ ነዋሪው አርሶ አደር ፈይሰል ኑረይን፤ በአካባቢው የተከናወነው የተፋሰስ ልማት አፈር እንዳይሸረሸርና አካባቢው እንዳይራቆት አድርጓል ሲሉ ተናግረዋል። የአካባቢያቸው ትልቁ ትኩረት በዝናብ ምክንያት ተሸርሽሮ የሚወርደው አፈር ወደ ግድቡ እንዳይደርስ መከላከል መሆኑን የጠቆሙት ደግሞ ሌላው የዚሁ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ፋንታሁን እጅጉ ናቸው። የግብርናው ዘርፍ ሃላፊዎች ደግሞ የተፋሰስ ልማቱ ከግብርና ልማትና ምርታማነት እንዲሁም ስነ ምህዳርን ከመጠበቅ ባለፈ ታላቁ የህዳሴ ግድብን ከደለል የተከላከለ መሆኑን ገልጸዋል።   የአቡራሞ ወረዳ የግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አታላይ ደረጀ፤ በህዳሴ ግድብ ዙሪያ በሚከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ሁሉም ግንዛቤን አግኝቶ እንዲሳተፍ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ ባበከር ሃሊፋ በክልሉ በሚገኙ ተፋሰሶች ላይ አርሶ አደሮች ተደራጅተው ሰፋፊ ሥራዎች መሰራታቸውን ገልጸዋል።   በዚህም አርሶ አደሩ ተጠቃሚ እየሆነና ግድቡ በደለል እንዳይሞላ አስተዋጽኦ ለማበርከት ጠንካራ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ታላቁ የአረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭን ስኬታማ ለማድረግ የጎላ አስተዋፅኦ ያበረክታል
May 13, 2025 175
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ታላቁ የአፍሪካ አረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭን ስኬታማ ለማድረግ የጎላ አስተዋፅኦ እንደሚያበረክት በአፍሪካ ህብረት የብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ዳይሬክተር ሃርሰን ኒያምቤ ገለፁ። በአፍሪካውያን የሚተገበረው ታላቁ የአረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭ የባለሙያዎች እና የአጋር አካላት ስብሰባ ዛሬ በአፍሪካ ህብረት ዋና መስሪያ ቤት መካሄድ ጀምሯል።   በአፍሪካ ህብረት የብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ዳይሬክተር ሃርሰን ኒያምቤ በዚሁ ጊዜ ለኢዜአ እንዳሉት ኢኒሼቲቩ በመላው አፍሪካ በዋናነት በሳህል ቀጣና በረሃማነትን እና የመሬት መራቆትን ለመከላከል የተቋቋመ ፕሮጀክት ነው። የረጅም ጊዜ ግብ የተጣለበት ፕሮጀክቱ ጉልህ ስኬቶችን እያስመዘገበ እንዳለም አንስተዋል። በቀጣናው በተጀመሩ የአረንጓዴ ልማት ሥራዎች አርብቶ አደሮች ለከብቶቻቸው መኖ እንዲያገኙ እያስቻሉ መሆኑን ጠቅሰው፥ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥም አስተዋፅኦ እያበረከተ ነው ብለዋል። ኢኒሼቲቩ የስራ እድል በመፍጠር በኩል ትልቅ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ነው ዳይሬክተሩ የገለጹት። የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ታላቁ የአረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭን ለማሳካት የሚያግዝ በመሆኑ ሌሎች ሀገራት ልምድ መውሰድ አለባቸው ብለዋል። ኢትዮጵያ መርሃ ግብሩን ወደ ሌሎች ሀገራት ለማስፋት የጀመረችውን ስራ በማድነቅ፥ ይበልጥ ሊጠናከር ይገባል ነው ያሉት።   የአፍሪካ የደን ፎረም ዋና ፀሐፊ ፕሮፌሰር ላቦዴ ፖፑላ በበኩላቸው ኢኒሼቲቩን በታሰበው ልክ ስኬታማ ለማድረግ ሁሉም ሀገራት በቁጠኝነት መስራት እንዳለባቸው ተናግረዋል።
በክልሉ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በአፈርና ውሃ ጥበቃ ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል
May 13, 2025 141
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2017(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በአፈርና ውሃ ጥበቃ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ። ክልሉ ለ2017 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መረሃ -ግብር ችግኞች ዝግጅት እያደረገ መሆኑን አስታወቀ። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ኤሊያስ ከድር ባለፉት አመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የአካባቢውን ስነ-ምህዳር መሰረት በማድረግ የተለያዩ ችግኞች መተከላቸውን አስታውሰዋል።   በዚህም በአፈርና ውሃ ጥበቃ፣ በግብርና ምርታማነትና በደን ሽፋን ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን አብራርተዋል። በበጋ የአፈርና ውሃ ጥበቃ መረሃ-ግብር ማህብረሰቡን በማሳተፍ ሰፊ ስራ መከናወኑን ገልጸው፤ በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ የአረንጓዴ አሻራ ግብን ለማሳካት እንደሚያግዝም ተናግረዋል። ለ2017 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መረሃ-ግብር ለምግብነት የሚውሉ ችግኞችን ጨምሮ የተለያዩ ችግኞችን እያዘጋጀ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የችግኝ ተከላ ቦታዎችን መለየትና ማዘመን እንዲሁም የመረጃ ተአማኒነትን ማረጋገጥ ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል። በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች እየተደረጉ ያሉ የችግኝ ዝግጅቶችና የተከላ ቦታዎች ልየታ በመስክ ጉብኝት ክትትል እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ህብረተሰቡ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በባለቤትነት እያደረገ ያለውን ተሳትፎ አጠናክሮ እንዲቀጥል ምክትል ሃላፊው ጥሪ አቅርበዋል።   የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሩ የሥራ እድል በመፍጠር ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ችግኝ በማፍላት የተሠማሩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተናግረዋል።
ክልሎቹ ለዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር በአይነትና በብዛት የችግኝ ዝግጅት እያደረጉ ነው
May 13, 2025 146
አዳማ፤ግንቦት 5/2017 (ኢዜአ)፦ለዘንድሮ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር በአይነትና በብዛት የችግኝ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች እና የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች አስታወቁ። በሁለቱ ክልሎች ለዘንደሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እየተደረገ ያለውን ዝግጅት በተመለከተ የኢዜአ ሪፖርተር የሚመለከታቸውን የስራ ሃላፊዎች አነጋግሯል። በምክትል ፕሬዝዳንት ማዕረግ የደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው፤ በዚህ ዓመት በክልሉ ቡናና ሻይ ቅጠል፣ፍራፍሬን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው በ420 ሚሊዮን ችግኞች ለተከላ ዝግጁ እየተደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። ከችግኝ ዝግጅቱ በተጓዳኝ የተከላ ቦታ ልየታ፣የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ቁፋሮ እና ሌሎችም አስፈላጊ ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆኑን አመላክተዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ባበክር ኸሊፋ፤ በክልሉ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 75 ሚሊዮን ችግኞችን ለመትከል እቅድ መያዙን ጠቅሰው፥ በዚህም መሰረት በአይነትና በብዛት ችግኞችን በማፍላት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በእስካሁኑ ሂደትም ችግኞች የሚተከሉትን ቦታ የመለየትና ማዘጋጀት እንዲሁም የችግኝ መትከያ ጉድጓድ ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የሚተከሉት ችግኞች ከተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ባለፈ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን ሃላፊዎቹ አስረድተዋል።
እየተከናወኑ የሚገኙ ዘላቂ የተፈጥሮ ሀብት ልማት ሥራዎች ለሥርዓተ ምህዳር መጠበቅ ወሳኝ ሚናን ይጫወታሉ
May 10, 2025 118
አዳማ፤ግንብት 2/2017 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እየተካሄዱ የሚገኙ ዘላቂ የተፈጥሮ ሀብት ልማት ሥራዎች ለሥርዓተ ምህዳር መጠበቅ እና ለምርትና ምርታማነት መጨመር ወሳኝ መሆናቸውን የኢትዮጵያ ደን ልማት አስታወቀ። የኢትዮጵያ ደን ልማት የአረንጓዴ አሻራና የተጎሳቆለ መሬት ማገገሚያ ልዩ ፈንድ ማስፈፀሚያ የአምስት ዓመት ማእቀፍ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ለመወያየት ያዘጋጀው መድረክ በአዳማ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ ላይ የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር አቶ ከበደ ይማም እንዳሉት፥በኢትዮጵያ እየተካሄዱ የሚገኙ ዘላቂ የተፈጥሮ ሀብት ልማት ሥራዎች ለሥርዓተ ምህዳር መጠበቅና ለምርትና ምርታማነት መጨመር ወሳኝ ናቸው። በተለይ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት አረንጓዴ አሻራ ተግባራዊ ከተደረገ ወዲህ እንደ ሀገር ከ40 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መትከል መቻሉን ያስታወሱት ዋና ዳይሬክተሩ፥ ከተተከሉት ውስጥ ከ35 እስከ 40 በመቶ የሚገመቱት የደን ችግኞች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። አሁን ላይም ለዓለማችንና ለሀገራችን ዋና ተግዳሮት የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥና የመሬት መራቆት ችግርን ለመቀልበስ የአረንጓዴ አሻራና የተጎዱ መሬቶች ማገገሚያ ልዩ ፈንድ አዋጅ ተደንግጓል ብለዋል። ይህ የመንግሥት ውሳኔ ኢትዮጵያ ዜጎቿን ከድህነት ለማውጣት ያላትን ከፍተኛ ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ አስታውቀዋል። የአረንጓዴ አሻራና የተጎሳቆለ መሬት ማገገሚያ ልዩ ፈንድ ሀገራችን ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የገባችውን የተባበሩት መንግሥታት የዘላቂ ልማት ግቦችን፣የተራቆቱ መሬቶች ማገገሚያ ጊዜን ለማሳካት ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል። የቀጠናው ልማት የተመሰረተው በእኛ ውሀ ነው ያሉት አቶ ከበደ፥ የውሀው መሰረት ደግሞ ደኖቻችን ናቸው ብለዋል። በመሆኑም በመንግሥት የተዘጋጀው የአረንጓዴ አሻራና የተጎዱ መሬቶች ማገገሚያ ልዩ ፈንድ ድንበር ተሻጋሪ አሻራ መሆኑን አስታውቀዋል። በገንዘብ ሚኒስቴር የአረንጓዴ አሻራና የተጎዱ መሬቶች ማገገሚያ ፕሮግራም ማዕቀፍ አስተባባሪ አቶ ዘሪሁን ጌቱ፥ በመድረኩ ላይ ባቀረቡት ሠነድ እንዳመላከቱት ልዩ ፈንዱ ለአረንጓዴ አሻራ ስራዎች ቋሚና ተቋማዊ ሥርዓት ያለው የፋይናንስ አቅም እንዲኖር ለማስቻል ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህም የአየር ንብረት ለውጥን በዘላቂነት የሚቋቋም እና ከአየር ንብረት ብክለት የፀዳ ኢኮኖሚን ለመገንባት የተያዘውን አገራዊ ራዕይ ለማሳካት የጎላ አስተዋፅኦ እንዳለው አስገንዝበዋል። የተጎሳቆለ መሬት መልሶ እንዲያገግም በማድረግ፣የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ደኖችን በመጠበቅና በመንከባከብ ለአገራችን ዘላቂነት ያለው ኢኮኖሚያዊ፣ማህበራዊና የሥነ ምህዳር ጥቅም እንዲሰጥ ማድረግ ወሳኝ መሆኑንም አውስተዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን ድርቅና የአካባቢ መራቆትን ለመከላከል በ99 ተፋሰሶች የልማት ስራ ተከናውኗል
May 10, 2025 101
ነጌሌ ቦረና፤ግንቦት 2/2017 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ቦረና ዞን ድርቅና የአካባቢ መራቆትን ለመከላከል የሚያስችል 99 ተፋሰሶችን መሰረት ያደረገ የተፋስስ ልማት ስራ መከናወኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በተፋሰስ ልማት ስራው ከ188 ሺህ በላይ የዞኑ ህዝብ መሳተፉ የተገለጸ ሲሆን ከ12 ሺህ ሄክታር በላይ የግጦሽ መሬት ከንክኪ መከለሉም ተገልጿል። በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ አልይ አረባ፣ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራው በዋናነት በአካባቢው በተደጋጋሚ የሚያጋጥመውን ድርቅና የአካባቢ መራቆት መከላከልን ታሳቢ ያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም በበጋ ወራት በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች 63 ሺህ ሄክታር መሬት የሚያካልል የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ ተከናውኗል ብለዋል፡፡ የተፋሰስ ልማት ስራው የማሳና የተራራ ላይ እርከን፣ የተለያዩ የውኃ አካላትንና ምንጭ ማጎልበት እንዲሁም ችግኝ ዝግጅትን ያካተተ እንደነበረ ገልጸዋል። በዚህም 99 ተፋሰሶችን መሰረት በማድረግ በተከናወነ ስራ ከ188 ሺህ በላይ ህዝብ መሳተፉን ገልጸው፥ ከችግኝ ዝግጅት ባለፈ 500 ሺህ የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች መዘጋጀታቸውንም ጠቅሰዋል፡፡ እንዲሁም ለበጋ ወራት አገልግሎት የሚሰጡ 12 የተለያዩ የውሀ አካላትን የማዘጋጀት ስራም የዚሁ አካል እንደነበር ጠቁመዋል፡፡ በተፋሰስ ልማት ስራው 10 ሺህ ሄክታር የሚጠጋ የግጦሽ መሬት ለመከለል ታቅዶ ከ12 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ከንክኪ መከለሉንም አንስተዋል። የዞኑ ነዋሪዎች በአመዛኙ በአርብቶ አደርነት ህይወታቸውን እንደሚመሩ ገልጸው፥ የተከለለው የግጦሽ ሳር መሬት ከ60 ሺህ በላይ የቤት እንስሳትን ተጠቃሚ ያደርጋል ብለዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያ የደን ሽፋን ላይ ከፍተኛ ለውጥ እያመጣ ነው
May 8, 2025 197
አዳማ፤ሚያዚያ 30/2017 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያ የደን ሽፋን ላይ ከፍተኛ ለውጥ እያመጣ መሆኑን የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር አቶ ከበደ ይማም ገለጹ። ኢዜአ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከደን ልማት አኳያ የሚያስገኘው ፋይዳ ዙሪያ ከኢትዮጵያ ደን ልማት እና ከአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ኮሚቴ ከፍተኛ አመራሮች ጋር ቆይታ አድርጓል። የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር አቶ ከበደ ይማም እንዳሉት፥ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚን ለመገንባት ከያዘቻቸው እቅዶች መካከል የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዋነኛው ነው። መርሃ ግብሩ ከዚህ በፊት በተፈጥሮ ደን ላይ ሲደርስ የነበረውን ጉዳት ከመከላከል ባለፈ የደን ሽፋንን እያሳደገ መምጣቱንም አመልክተዋል። ከዚህ ቀደም በተፈጥሮ ደኖች ላይ ከፍተኛ ጭፍጨፋ ሲደርስ እንደነበር አስታውሰው፥ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተግባራዊ መደረግ ከጀመረ ወዲህ ግን የማገዶና የግንባታ ግብዓት ፍላጎትን ከማሟላት ባሻገር በደን ሀብት ላይ የሚደርሰው ጉዳት በእጅጉ እንዲቀንስ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን አብራርተዋል። መርሃ ግብሩ የአፈር መሸርሸርን በመከላከል ግድቦች በደለል እንዳይሞሉ ከማድረግ ባለፈ ወንዞች ዓመቱን ሙሉ ተመጣጣኝ ፍሰት እንዲኖራቸው ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ማስገኘቱን አውስተዋል። በተለይም ሥነ ምህዳር እንዲጠበቅና የእርሻ መሬት ከጎርፍ እንዲጠበቅ ጉልህ ሚና ማበርከቱን ጠቅሰው፥ በየዓመቱ 92 ሺህ ሄክታር ደን ላይ ሲደርስ የነበረውን ጭፍጨፋ ባለፈው ዓመት በተጠናው ጥናት መሠረት ወደ 27 ሺህ ሄክታር በመቀነሱ ከፍተኛ ስኬት መሆኑን አቶ ከበደ አስታውቀዋል። በተለይ የሚተከለው ችግኝ በውጭ ምንዛሬ የሚገባውን የጣውላና ሌሎች የእንጨት ምርትን በመተካት ረገድ ተስፋ የሚጣልበት ነው ሲሉ አስረድተዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ቴክኒክ ኮሚቴ ሰብሳቢ አደፍርስ ወርቁ(ዶ/ር) በበኩላቸው፥ በመርሃ ግብሩ ባለፉት ዓመታት ከተተከሉት ችግኞች ውስጥ የሀገሪቱን የደን ሽፋን ለማሳደግ የሚያስችሉ ከ40 እስከ 48 በመቶ የሚሆኑት የደን ዝርያዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህም ብዝሃሕይወት እንዳይጠፋ፣ የደን ሽፋን በማሳደግ እና ሀገር በቀል ዕፅዋት ዝርያዎችን ጠብቆ ለመጪው ትውልድ ለማስተላለፍ ምትክ የለሽ መሆኑን አውስተዋል። መርሃግብሩ ለኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪው የሚያስፈልጉ የእንጨት ግብዓቶችን ሳይንሳዊ በሆነ ዘዴ ለማምረት ጭምር ጠቀሜታ እንዳለው አስረድተዋል። ከዘላቂ ደን ልማት አንጻርም ዘንድሮ ለመትከል ከተዘጋጁት ችግኞች ውስጥ 2 ነጥብ 3 ቢሊዮን የሚሆኑት ሀገር በቀል የደን ዛፍ ዝርያዎች እንዲሆኑ ትኩረት መሰጠቱን አስረድተዋል። ይህም ትልቅ ስኬት መሆኑን ጠቁመው፥ በተለይ ሊጠፉ የተቃረቡና የተመናመኑ ሀገር በቀል የዕፅዋት ዝርያዎችን በመታደግ አካባቢያዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እንዳለው አደፍርስ(ዶ/ር) ገልጸዋል።
የዲጂታል መረጃ ስርዓቱ የአየር ንብረት ለውጥን የመከላከል አቅም መገንባት ያስችላል- ሚኒስትር ዴኤታ መለሰ መኮንን (ዶ/ር)
May 6, 2025 260
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 28/2017(ኢዜአ)፦ ለአርሶ አደሮች ስለ አየር ንብረት ሁኔታ መረጃ የሚሰጠው ዲጂታል ስርዓት የአየር ንብረት ለውጥን የመከላከል አቅም ለመገንባት ቁልፍ ሚና እንዳለው የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለሰ መኮንን (ዶ/ር) ገለጹ። የመረጃ አገልግሎት ስርዓቱን ለመቋቋም የተዘጋጀ የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና ስብሰባ ዛሬ በቢሾፍቱ ከተማ መካሄድ ጀምሯል። ውይይቱ በምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) እና በምግብ ዋስትና ላይ የሚሰራው ዓለም አቀፍ ጥምረት (CGIAR) ስር ያለው የአየር ንብረት ምርምር ፕሮጀክት (AICCRA) በጋራ ያዘጋጁት ነው። ስርዓቱ የተቀናጀ የአየር ንብረት ለውጥ መረጃን ከግብርና ዘርፍ ውሳኔ አሰጣጥ ጋር በማጣመር አርሶ አደሮች የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን መቋቋም የሚችሉበት አቅም መገንባትን አልሟል። በሞባይል እና ድረ ገጽ አማራጭ የሚሰራው ይህ ስርዓት ለአርሶ አደሮች ዘር የሚዘሩበትን ወቅት፣ የሰብል አይነት መረጣ እና የምርት መሰብሰቢያ ጊዜን የተመለከቱ መረጃዎችን የአየር ትንበያ፣ የአየር ንብረት መረጃ እና የሰብል ባህሪያትን መሰረት በማድረግ የሚሰጥ ነው። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለሰ መኮንን (ዶ/ር) የዲጂታል ስርዓቱ የአየር ንብረት ለውጥ ፈተናዎችን ከመቋቋም ባሻገር አስቀድሞ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል እንደሆነ ገልጸዋል። የመረጃ ስርዓቱ የአፈር ጤና፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይገበር እና የካርቦን ልህቀትን በመቀነስ የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ የሚቻልበትን ዘዴ እና አቅም መገንባትን ጨምሮ በሌሎች ቁልፍ ጉዳዮች ላይ የእውቀት እና የመረጃ ልውውጥ ማድረግ እንደሚያስችል ጠቁመዋል። የዲጂታል አሰራሩ የዘርፉ ተዋንያን የምግብ ዋስትት እና ዘላቂነትን አስመልክቶ ሙያዊ ምልከታቸውን የሚሰጡበትና መረጃ የሚያገኙበት ቋት እንደሆነም ነው ያስረዱት። ስርዓቱን በተቀናጀ ሁኔታ በመጠቀም የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል በጋራ መስራት እንደሚገባም አሳስበዋል። የኢጋድ የከባቢ አየር እና የተፈጥሮ ሀብቶች ዳይሬክተር ዳሄር ኤልሚ ሁሴን በበኩላቸው፥ በዓለም ባንክ የገንዘብ ድጋፍ የሚተገበረው ፕሮጀክት ለሰባት ዓመት እንደሚቆይ እና የምግብ ስርዓትን ለማጠናከር ወሳኝ አብክሮ እንዳለው ተናግረዋል። በውይይቱ ላይ የዲጂታል ስርዓቱ ይፋ እንደሚሆን ጠቁመዋል። በኢትዮጵያ የኢጋድ ተጠሪ አበባው ቢሆነኝ ኢጋድ የምግብ እና ስርዓተ ምግብ ደህንነትን ለማረጋገጥ፣ የዘላቂ የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም ለመፍጠር እና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም ለመገንባት በቁርጠኝነት እየሰራ ነው ብለዋል። የአገልግሎቱ ይፋ መሆን የኢጋድ ትልዕኮን ለማሳካት እንደሚያግዝ አመልክተዋል። ቀጣናዊው ስብስባ እስከ ሚያዚያ 29 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚቆይ የኢጋድ መረጃ ያመለክታል።
የኢንቨስትመንትና የልማት ፕሮጀክቶች የአካባቢ ብክለትን መከላከል ታሳቢ ያደረገ የምርት ሂደት እንዲከተሉ እየተደረገ ነው
May 5, 2025 187
አዳማ፤ ሚያዝያ 27/2017(ኢዜአ) - የኢንቨስትመንትና የልማት ፕሮጀክቶች የአካባቢ ብክለትን መከላከል ታሳቢ ያደረገ የምርት ሂደት እንዲከተሉ ጠንካራ ክትትልና ቁጥጥር እያደረጉ መሆኑን ኢዜአ ያነጋገራቸው የአማራ ክልልና የድሬደዋ ከተማ አስተዳደር የዘርፉ ሃላፊዎች ተናገሩ። የአማራ ክልል የአካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን የአካባቢና አየር ንብረት ለውጥ ዳይሬክተር አቶ አወቀ ይታይ፣ እንዳሉት ትራንስፖርት፣ የኢንዱስትሪ ተረፈ ምርቶች፣ የድምፅና ሌሎች በካይ ነገሮች ለአካባቢ ብክለት ምክንያት መሆናቸውን ተናግረዋል። በክልሉ በርካታ ኢንዱስትሪዎች መኖራቸውን ጠቅሰው እነዚህ የኢንቨስትመንትና የልማት ፕሮጀክቶች የአካባቢ ብክለትን ታሳቢ ያደረገ የምርት ሂደት እንዲከተሉ ክትትልና ቁጥጥር መጠናከሩን አስረድተዋል። ችግሩን ለመቀነስም ለባለድርሻ አካላት ስልጠና መስጠትና ስለ ጉዳቱ በቂ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ተከታታይ ግንዛቤ ማሳደጊያ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ኢንዱስትሪዎች ከግንዛቤ ባሻገር ብክለትን መቀነስ የሚያስችሉ አማራጭ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀም እንዲችሉ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። ከዚህም ባለፈ አሰራርና ተጠያቂነትን የሚያሰፍኑ የህግ ማዕቀፎች፣ ደንቦች፣ መመሪያዎችና የማስፈፀሚያ ስልቶች እየተዘጋጁ መሆኑን ተናግረዋል። በተመሳሳይ የድሬደዋ ከተማ አስተዳደር የአከባቢ፣ ደንና ዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን ዳይሬክተር አቶ ደረጀ አቢቲ፤ በአስተዳደሩ የአካባቢ ድምፅና የውሃ አካላት ብክለት ቅድመ መከላከል ትኩረት ማግኘታቸውን ገልጸዋል። በተለይም ኢንዱስትሪዎችን ጨምሮ የልማት ፕሮጄክቶችና የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት ህገ እና ደንብ አክብረው እንዲሰሩ ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። በከተማው የሲሚንቶ ፋብሪካዎችን ጨምሮ ሌሎች የልማት ተቋማት የአካባቢ ብክለትን በሚቀንስ መልኩ የልማት ስራቸውን እንዲያከናውኑ በየጊዜው ክትትልና ቁጥጥር በማድረግ የእርምት እርምጃ እየተወሰደ መሆኑንም ገልጸዋል። የድምፅና የውሃ አካላት ብክለት ለመከላከልም ክትትልና ቁጥጥር እየተደረገ መሆኑን ጠቅሰው፤ የታዳሽ ሃይል በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ድጋፍና የማበረታታት ስራዎች እንደሚሰሩም አስረድተዋል። በተጨማሪም የከተማዋ የአረንጓዴ ልማት ስራ በተለይም በአፈርና ውሃ ዕቀባ፣ በደን ልማት እንዲሁም ከንኪኪ ነፃ አካባቢን በመፍጠር ረገድ በአስተዳድሩ የተሻለ ስራ እየተከናወነ መሆኑንም ገልጸዋል። የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ጫናን ለመቋቋም የተናበበና የተቀናጀ ምላሽ ትግበራ ላይ ያተኮረ ውይይት ከሰሞኑ በአዳማ መካሄዱ ይታወሳል።      
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በዘላቂነት ለመግታት ውጤታማ ተግባራትን አከናውናለች-ሚኒስቴሩ
May 2, 2025 271
አዳማ፤ሚያዝያ 24/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በዘላቂነት ለመግታት የሚያስችል ውጤታማ ተግባራትን ማከናወኗን የፕላንና ልማት ሚኒስቴር አመለከተ። ከፌዴራልና ከክልሎች አካባቢ ጥበቃ ሴክተሮችና ከሚኒስቴሩ የተወጣጡ የስራ ኃላፊዎች የተሳተፉበት የዘጠኝ ወራት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ምላሽ ትግበራ ዕቅድ ግምገማ መድረክ በአዳማ በመካሄድ ላይ ይገኛል። በሚኒስቴሩ የተናበበና የተቀናጀ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ምላሽ ትግበራ ብሄራዊ አስተባባሪ ሙክታር አቡኬ (ዶ/ር) እንደገለፁት፥ ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በዘላቂነት ለመግታት ውጤታማ ተግባራትን አከናውናለች። በዚህም የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመከላከል የአረንጓዴ አሻራ፣ የብሔራዊ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ እቅዶች ትግበራ እና በአየር ንብረት ለውጥ ለሚደርስ ጉዳት እና ኪሳራ የሚከፈል የፋይናንስ ፈንድ ማዕቀፍ ላይ ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱን ገልፀዋል። በተለይ ሀብት የማሰባሰብ፣የፖሊሲ እና የማስፈፀሚያ ስትራቴጂዎች፣ አሰራሮችና የህግ ማዕቀፎችን የማበጀት ስራ በውጤታማነት መከናወኑን አንስተዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ስዩም መኮንን በበኩላቸው፥ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ጉዳት እያየለ መጥቷል። ድርቅ፣ጎርፍ፣የበረሃ አንበጣ፣የመሬት መንሸራተት በተደጋጋሚ ጊዜ እያጋጠመ መሆኑን ጠቅሰው፥ይህም በግብርና ምርትና ምርታማነት፣ በእንስሳት ሀብት፣በመሰረተ ልማትና በሀይል አቅርቦት ላይ ተፅዕኖ እያሳደረ መሆኑን ተናግረዋል። ሀገሪቷ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የጀመረቻቸው አዳዲስ ኢንሺዬቲቮች ውጤታማ እንዲሆኑ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ እውን ማድረግ ላይ መረባረብ እንደሚገባም አመልክተዋል። ለዚህም የተናበበና የተቀናጀ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ምላሽ ትግበራን ውጤታማ ለማድረግ በየደረጃው ያሉ የባለድርሻ አካላት ርብርብ ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል። ለዚህም ሲባል መንግስት ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የተናበበና የተቀናጀ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችሉ ፖሊሲና ስትራቴጂን በመቅረጽ እንዲሁም አሰራሮችና የህግ ማዕቀፎች እየዘረጋ መሆኑን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም