ቀጥታ፡
አካባቢ ጥበቃ
ባለፈው ክረምት በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞችን እየተንከባከብን ነው - አርሶ አደሮች
Nov 18, 2025 54
አምቦ፤ ህዳር 9/2018(ኢዜአ)፡- ባለፈው ክረምት በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞችን እየተንከባከቡ መሆኑን የምዕራብ ሸዋ ዞን አርሶ አደሮች ተናገሩ። አርሶ አደሮቹ ከዚህ ቀደም በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በተተከሉ ችግኞች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እያገኙ መሆናቸውን ጠቁመው ዘንድሮም በችግኝ እንክብካቤው ላይ አተኩረዋል።   ከጨሊያ ወረዳ አርሶ አደሮች መካከል አስፋው ድንቁ ባለፉት ዓመታት በተከናወነ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተራቆተ እና የተጎዳ ማሳቸው አገግሞ አሁን ላይ በፊት ከሚያገኙት ምርት በእጥፍ እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም የእርሻ ማሳቸው በጎርፍ ተጠርጎ ምርታማነቱ በመቀነሱ ስጋት ውስጥ ገብተው እንደነበረም አስታውሰዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ በተከታታይ በተተከሉ ችግኞች የአፈር መሸርሸር በመቀነሱ የእርሻ ማሳቸው ምርታማነቱ መጨመሩን አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅት የተለያዩ የጥራጥሬ ሰብሎችን እያለሙ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው የተተከሉ ችግኞች የመሬቱን ለምነት የሚጠብቁ በመሆኑ ለከብቶቻቸው መኖ ማግኘታቸውንና አካባቢያቸውም መልካም ገጽፅታ መላበሱን አውስተዋል።   ሌላው አርሶ አደር ፋይሳ ቀነኒ በበኩላቸው፣ በአካባቢያቸው የተጎዳ መሬት በአረንጓዴ ዐሻራ ልማት እንዲያገግም በመደረጉ ከዚህ ቀደም ከሚያለሙት የጥራጥሬ ሰብሎች በተጨማሪ ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኞችን በመትከል ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን አንስተዋል፡፡ መርሃ ግብሩ ከመጀመሩ በፊት ዝናብ ወቅቱን ጠብቆ ስለማይዘንብ ብዙ መቸገራቸውን አስታውሰው አሁን ላይ ግን ዝናቡም ወቅቱን ጠብቆ በመዝነቡ ምርታማነታቸው ጨምሮ የተሻለ ገቢ እያገኙ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ አርሶ አደሮቹ የአካባቢያቸውን ማህበረሰብ በማስተባበር የእርከን ስራ ላይ የአፈር ለምነት እንዲጠብቅና የተተከሉ ችግኞች እንዲጸድቁ ለተከታታይ ዓመታት በሰሩት ስራ ለውጥ መመዝገቡን ተናግረዋል።   የጨሊያ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርናና መሬት አስተዳዳር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኢነዑ ተሾመ በበኩላቸው፤ በወረዳው በሚከናወነው የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ስራ የህብረተሰቡ ተሳትፎ እያደገ መጥቷል ብለዋል፡፡ በወረዳው በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ለተተከሉት ችግኞች አስፈላጊው እንክብካቤ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በወረዳው የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ከተጀመረ ወዲህ የአካባቢው ስነ ምህዳር ከመቀየሩም በላይ የአርሶ አደሮቹ ምርትና ምርታማነት መጨመሩን አመልክተዋል። በወረዳው በአረንጓዴ ዐሻራ ልማት መርሃ ግብር ከሃገር በቀል የዛፍ ችግኞች በተጨማሪ ለምግብነት የሚውሉ ማንጐ፣ ሙዝ፣ አቮካዶ እና ቡና ጭምር መተከላቸውን ተናግረዋል፡፡
ሰውና ተፈጥሮ የተዋደዱበት ቆጠር ገድራ  ጥብቅ ደን
Nov 18, 2025 49
ሰውና ተፈጥሮ የተዋደዱበት ቆጠር ገድራ በጉራጌ ዞን ከሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎች መካከል አንዱ ነው። ጥብቅ ደኑ ከጉራጌ ዞን ከወልቂጤ ከተማ በ42 ኪሎ ሜትር ርቀት በስተምሥራቅ በእዣ ወረዳ ቆጠር ገድራ ቀበሌ ይገኛል።   ጥብቅ ደኑ በበርካታ ሀገር በቀል ዛፎች የተሸፈነ፣ ሰውና ተፈጥሮ የተዋደዱበት፣ ለአካባቢው ማህበረሰብ የህይወት እስትንፋስ ነው። የቆጠር ገድራ ጥብቅ ደን ቀልብን የሚስብ፣ ነፍስ በሀሴት የምትሞላበት፣ መንፈስ የሚታደስበት ውብ ስፍራ ነው። ቆጠር ገድራ ተዳፋታማ በሆነ ስፍራ የሚገኝ ሲሆን ብዛት ባላቸው ሀገር በቀል ዛፎች ማለትም ዝግባ፣ የኮሶ ዛፍ፣ የሀበሻ ፅድ የተሞላ ነው፡፡   የቆጠር ገድራ የተፈጥሮ ደን ለረጅም ዘመናት ከሰው ንክኪ ተጠብቆ የቆየው በአካባቢው ኅብረተሰብ ነባር ባህል መሠረት የጥንት አባቶች ደኑ እንዳይቆረጥ በቃል ኪዳን/ጉርዳ/ ስለተሳሰሩ መሆኑም ተገልጿል፡፡ 20ኛው የብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀንን ምክንያት በማድረግ ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተውጣጣ የጋዜጠኞች ቡድን በጉራጌ ዞን ከሚገኙ የቱሪዝም መዳረሻዎች አንዱ የሆነውን የቆጠር ገድራ ጥብቅ ደንን ጎብኝቷል።   የእዣ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ዘውዱ ዱላ በጉብኝቱ ወቅት እንደገለጹት ከጥንት ጀምሮ በአካባቢው ማህበረሰብ ዘንድ ደን መቁረጥ እንደ ወንጀል የሚቆጠር፤ በአካባቢው ባህል የሚያስቀጣ ነውር ተግባር ነው፡፡ ጥብቅ ደኑ ከ350 ሄክታር መሬት በላይ እንደሚሸፍን እና በውስጡ ከ18 በላይ የዛፍ ዝርያዎች እንደሚገኙም አንስተዋል። የዞኑ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ መሰረት አመርጋ በበኩላቸው የጉራጌ ህዝብ በስራ ወዳድነቱና ታታሪነቱ የሚታወቅ ከተፈጥሮ ጋር ትልቅ ቁርኝት ያለው መሆኑን ተናግረዋል። በጉራጌ ዞን እዣ ወረዳ የሚገኘው የቆጠር ገድራ ጥብቅ የተፈጥሮ ደን ከ700 ዓመታት በላይ እንዳስቆጠረ የሚነገርለት ሲሆን ህብረተሰቡ ደኑን ጠብቆ ያቆየበት መንገድ ከተፈጥሮ ጋር ላለው ቁርኝት አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል። ደኑን በዘላቂነት ጠብቆ በማቆየት አካባቢውን የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግናና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሠራ መሆኑንም ተናግረዋል።   ቆጠር ገድራ ጥብቅ ደን በውስጡ ከያዛቸው የዛፍ ዝርያዎች ባለፈ የበርካታ ብዝኃ ህይወት መኖሪያ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የእዣ ወረዳ ደን እና አካባቢ ጥበቃ ልማት ጽህፈት ቤት የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ሂደት አስተባባሪ ብርሃኑ ብርሼ ናቸው። እንደዚህ ዓይነት ጥብቅ ደኖች ሥነ ምሕዳርን በመጠበቅ ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ተያይዘው የሚመጡ ችግሮችን ለመከላከል ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታሉ ብለዋል።
ኢትዮጵያ (ኮፕ 32)ን እንድታስተናግድ መመረጧ ለአየር ንብረት ለውጥ እርምጃ ላላት ጽኑ ቁርጠኝነት እውቅና የሰጠ ነው - ኢጋድ
Nov 15, 2025 95
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 32)ን እንድታስተናግድ መመረጧ ለአየር ንብረት ለውጥ እርምጃና አረንጓዴ ልማት ቁርጠኝነቷ እውቅና የሰጠ መሆኑን የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) ገለጸ። የድርጅቱ ዋና ጸሀፊ ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) ኢትዮጵያ ኮፕ 32 እንድታዘጋጅ መመረጧን ተከትሎ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ጉባኤውን ማዘጋጀቷ በአየር ንብረት እና ልማት ያላት መሪነት እያደገ መምጣቱን የሚያሳይ ነው ብለዋል። የአካባቢ ስነ ምህዳርን ወደ ነበረበት የመመለስ፣ ዘላቂ እድገትና የማይበገር አቅም ለመገንባት ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት የሚያመላክትና ለዚህም ስራዋ እውቅና የሰጠ መሆኑን አመልክተዋል። አረንጓዴ ዐሻራ እና የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ አረንጓዴ ልማት ስራ ማሳያዎች እንደሆኑም ነው የተናገሩት። ኮፕ 32 ለኢጋድ ቀጣና ወሳኝ መድረክ መሆኑን ገልጸው ተቋሙ ድርቅ፣ የአየር ንብረት ለውጥ የፈጠረው የዜጎች መፈናቀልና የውሃ እጥረትን ጨምሮ ሌሎች አንገብጋቢ አጀንዳዎች የበለጠ ትኩረት እንዲሰጣቸው እንደሚያደርግ አመልክተዋል። ኢጋድ ከኢትዮጵያ፣ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ማዕቀፍ ጽህፈት ቤት(UNFCCC Secretariat) እና ዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በመሆን ጉባኤው ሁሉን አሳታፊ፣ የአፍሪካ የቅድሚያ ትኩረቶች ማዕከል ያደረገና ለአየር ንብረት ለውጥ ዘላቂ መፍትሄ የሚገኝበት እንዲሆን በትብብር እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። በብራዚል ቤለም እየተካሄደ የሚገኘው 30ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 30) ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2027 የሚካሄደውን ኮፕ 32 ጉባኤ እንድታስተናግድ መመረጧ ይታወቃል። የአፍሪካ ሀገራት ለኢትዮጵያ የኮፕ 32 የማስተናገድ ፍላጎት ሙሉ ይሁንታቸውን ሰጥተዋል።
ኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 32)ን እንድታስተናግድ መመረጧ ለኢትዮጵያ እና ለአፍሪካ ታሪካዊ ነው - የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር
Nov 15, 2025 102
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 32)ን እንድታስተናግድ መመረጧ ለኢትዮጵያ እና ለአፍሪካ ታሪካዊ ነው ሲሉ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። ሊቀ መንበሩ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ32)ን እንድታስተናግድ በመመረጧ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ጉባኤውን የማስተናገድ ውሳኔው ለኢትዮጵያ እና ለአፍሪካ ታሪካዊ መሆኑን ሊቀመንበሩ ገልጸው ይህም አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ እርምጃ ያላትን የማይናወጥ ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል። ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አማካኝነት እያሳየች ያለውን የአየር ንብረት የመሪነት ሚናም አድንቀዋል። ኢትዮጵያ መጠነ ሰፊ የደን መልሶ ልማት እና አረንጓዴ ዐሻራን ጨምሮ ጠንካራ የአካባቢ ጥበቃ እርምጃዎችን እየወሰደች እንደምትገኝ አመልክተዋል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ሁነቶችን በስኬት በማስተናገድ እምቅ አቅም እንዳላት አንስተው ከፍተኛ ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ ጉባኤዎችን ለማዘጋጀት ጠንካራ ተቋማዊ አቅም እና ልምድ አላት ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት ዋና መቀመጫ እና የዓለም የዲፕሎማሲ ማዕከል የሆነችው አዲስ አበባ ጉባኤውን እንድታስተናግድ መመረጧ በዓለም አቀፍ ትብብር ያላትን ማዕከላዊ ሚና የበለጠ እንደሚያሳድገውም ገልጸዋል። ኮሚሽኑ ከኢትዮጵያ፣ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ማዕቀፍ(UNFCCC) እና አጋሮች ጋር በመሆን(ኮፕ 32) ሁሉን አካታችና ውጤታማ በማድረግ የአፍሪካን የአየር ንብረት የቅድሚያ ትኩረቶች የበለጠ ለማራመድና ዓለም አቀፍ አጋርነት ለማጠናከር በቅርበት እንደሚሰራ መግለጻቸውን ህብረቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል። በብራዚል ቤለም እየተካሄደ የሚገኘው 32ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 30) ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2027 የሚከናወነውን ኮፕ 32 እንድታስተናግድ ተመርጣለች። የአፍሪካ ሀገራት ለኢትዮጵያ የኮፕ 32 የማስተናገድ ፍላጎት ሙሉ ድጋፋቸውን መስጠታቸው ይታወሳል።
ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የጋራ ርምጃን የሚያበረታታ ውጤት ለማምጣት ቁርጠኛ ናት - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Nov 14, 2025 132
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ በኮፕ 32 መድረክ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የጋራ ርምጃን የሚያበረታታ ጠንካራ እና ትርጉም ያለው ውጤት ለማምጣት ሙሉ በሙሉ ቁርጠኛ መሆኗን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አረጋገጡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ ኮፕ 32ን እንድታስተናግድ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ትልቅ ኃላፊነት ስለሰጠን ክብር ይሰማናል ብለዋል። አፍሪካ በ2025 በተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ኮንፈረንስ (COP 30) ላይ በብራዚል በአንድ ድምጽ ተናግራለች፤ ዓለምም አዳምጧል ብለዋል። እንዲሁም ኢትዮጵያ በፈረንጆቹ በ2027 በአዲስ አበባ COP 32ን ለማስተናገድ ያቀረበችውን ጥያቄ ሙሉ በሙሉ ለደገፉ የአፍሪካ ሀገራት ተወካዮች ምሥጋና አቅርበዋል። በሰው ልጆች ኑሮ በጣም አንገብጋቢ ከሆኑት ተግዳሮቶች መካከል አንዱን ለመቅረፍ እንዲቻል የጋራ ጥረቶችን ለመምራት ዕድሉን ስላገኘንም አመሥጋኞች ነን ብለዋል። ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ይህን ትልቅ ኃላፊነት ስለሰጠንም ክብር ይሰማናል ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ይህ ዕውቅና ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ላይ ያላትን ቁርጠኛ ርምጃ፣ አመራር ብሎም ዋና ዋና ዓለም አቀፍ ዝግጅቶችን የማስተናገድ የዳበረ ዐቅም ያሳያል ሲሉም በአጽንኦት ገልጸዋል። በመሆኑም ኢትዮጵያ በምታስተናግደው የኮፕ 32 መድረክ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የጋራ ርምጃን የሚያበረታታ ጠንካራ እና ትርጉም ያለው ውጤት ለማምጣት ሙሉ በሙሉ ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች ላይ የበጋው ደረቅ፣ፀሐያማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ ይቀጥላል
Nov 12, 2025 159
አዲስ አበባ፤ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦በሚቀጥሉት አስር ቀናት በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች ላይ የበጋው ደረቅ፣ፀሐያማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፥ በሰሜን፣በሰሜን ምስራቅ፣ በምስራቅ፣ መካከለኛው እና ደቡብ ደጋማ አካባቢዎች ላይ የሌሊቱና የማለዳው ቅዝቃዜ እንደሚቀጥል አስታውቋል። በጋ ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው የሆኑት የደቡብ፣ደቡብ ምስራቅ እና የደቡብ ምዕራብ የአገሪቱ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ የሚቲዎሮሎጂ መረጃዎች ያሳሉ ብሏል። ወቅቱን ያልጠበቀ አነስተኛ መጠን ያለው ዝናብ በሰሜን፣ መካከለኛው፣ ምዕራብና ደቡብ ጎንደር ዞኖች፣ባህርዳር ዙሪያ፣ አዊ፣ በምዕራብና ምስራቅ ጎጃም፣ መተከል፣ አሶሳ፣ ካማሺ፣አርሲ፣በባሌ ዞኖች አልፎ አልፎ ሊዘንብ እንደሚችል ኢኒስቲትዩቱ ገልጿል። በሚቀጥሉት አስር ቀናት በደቡብ ምዕራብ እና ደቡባቢ የአገሪቱ ክፍሎች ላይ የሚኖረው መካከለኛ መጠን ያለው ርጥበት ለወቅቱ የግብርና ስራ እንቅስቃሴ በአመዛኙ አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው አስታውቋል። የበጋ ርጥበት ተጠቃሚ ተፋሰሶች መጠነኛ የገፀ ምድር የውሃ ፍሰት እንደሚኖራቸው የሚጠበቅ ሲሆን የተቀሩት ዝቅተኛ ርጥበት እንደሚኖራቸው ገልጿል። በዚህም አብዛኛው ባሮ አኮቦ፣ መካከለኛው እና ታችኛው ኦሞ ጊቤ፣ ስምጥ ሸለቆ፣ አባይ እንዲሁም ገናሌ ደዋ መካከለኛ ርጥበት ያገኛሉ፡፡ አብዛኛው አዋሽ፣ዋቤ ሸበሌ፣አፋር ደናክል፣ተከዜ፣ ኦጋዴን ደግሞ ከመጠነኛ ርጥበት እስከ ደረቅ ሁኔታ ይኖራቸዋል ተብሏል።
ኢትዮጵያ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ እንድታስተናግድ ተመረጠች
Nov 12, 2025 177
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 32) እንድታስተናግድ ተመርጣለች። 30ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 30) በብራዚል ቤለም እየተካሄደ ይገኛል። ኢትዮጵያ በስብሰባው ላይ ኮፕ 32ትን የማስተናገድ ጥያቄ በይፋ ያቀረበች ሲሆን የአፍሪካ ሀገራት ጉባኤውን እንድታስተናግድ ድጋፍ ሰጥተዋታል። የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተደራዳሪዎች ቡድን ሊቀ መንበር ሪቻርድ ሙዩንጊ ቡድኑ የኢትዮጵያን የኮፕ 32 የማስተናገድ ጥያቄ ተቀብሎ ማጽደቁን ለኤኤፍፒ ገልጸዋል።   የኮፕ 30 ፕሬዝዳንት የሆነችው ብራዚልም የአፍሪካ ሀገራት ኢትዮጵያን መምረጣቸውን አረጋግጣለች። የተደራዳሪ ቡድኑ መደበኛ ያልሆነ ውሳኔ በሁሉም የጉባኤው ተሳታፊ ሀገራት መጽደቅ እንደሚጠበቅበት እና ይህም ኮፕ 30 በሚጠናቀቅበት ህዳር 12 ቀን 2018 ዓ.ም ይፋ ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተገልጿል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ አስተናጋጅነት በድርጅቱ ስር ባሉ አምስት ቀጣናዎች ውስጥ ያሉ ሀገራት በመፈራረቅ የሚያዘጋጁት ነው። ብራዚል የላቲን እና የካሪቢያን ሀገራት ወክላ መመረጧን ተከትሎ ኮፕ 30ን እያካሄደች ትገኛለች። ኮፕ 30 እስከ ህዳር 12 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
ኢትዮጵያ ዓለም አቀፉን ጉባዔ ለማስተናገድ ከአፍሪካ ሙሉ ድጋፍ አገኘች
Nov 11, 2025 194
አዲስ አበባ፤ ህዳር 2/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ እንድታስተናግድ ከአፍሪካ ሀገራት ሙሉ ድጋፍ አግኝታለች። በብራዚል ቤሌም እየተካሄደ የሚገኘው 30ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ መደበኛ ጉባዔውን እያካሄደ ነው። አስቀድሞ በመሪዎች ስብሰባ በጀመረው ጉባዔ ላይ ኢትዮጵያ 32ኛውን የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔን በአዲስ አበባ ለማዘጋጀት ፍላጎቱም ዝግጁነቱም እንዳላት መግለጿ ይታወሳል። አስቀድሞ በርካታ የጎንዮሽ ውይይቶችን ሲያካሂድ ቆይቶ፥ ቴክኒካዊ ድርድርና ውይይቶችን በሚያስተናግደውና ትላንት በጀመረው ጉባዔ ላይ የኢትዮጵያን ጥያቄ የአፍሪካ ሀገራት መስማማታቸውን ይፋ ማድረጋቸውን የኢቢሲ ዘገባ ያመላክታል። የወቅቱ የአፍሪካ ተደራዳሪዎች ቡድን ሊቀመንበር በሆነችው ታንዛኒያ በኩል የኢትዮጵያ ጥያቄ ተቀባይነት ማግኘቱ ተገልጿል። ይህንኑ አስመልክቶ በጉባዔው ንግግር ያደረጉት በብራዚል ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ልዑልሰገድ ታደሰ ኢትዮጵያ ጉባዔውን ለማስተናገድ ያቀረበችውን ጥያቄ አፍሪካውያን በመደገፋቸው ኢትዮጵያ ትልቅ አክብሮት አላት፣ እንደምታሳካው መተማመናቸውም አስደሳች ነው፣ ለዚህም ኢትዮጵያ ታመሰግናለች ማለታቸውንም አስነብቧል። አዲስ አበባ እንግዶቿን በሚመጥን ደረጃ ጉባዔውን ለማስተናገድ ዝግጁ መሆኗን ያረጋገጡት አምባሳደሩ፥ ለኢትዮጵያ ጥያቄ ሌሎች ሀገራትም ድጋፍ እንዲሰጡ ጥሪ አቅርበዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ዳፋን ለመከላከል እየወሰደቻቸው ያሉ ተግባራዊ እርምጃዎች፣ አዲስ አበባ 2ኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔን ጨምሮ ታላላቅ ዓለም አቀፍ ኮንፍረንሶችን በስኬት ማስተናገዷ፣ እንዲሁም በሁሉም ረገድ ያላትን ዝግጁነት በመግለጽ ጥያቄዋን ለዘንድሮው ጉባዔ በይፋ ማቅረቧ ይታወሳል። አምባሳደር ልዑልሰገድ ታደሰ ኢትዮጵያ አሁንም የአየር ንብረት ለውጥን የመቋቋም ተግባራዊ እርምጃዎችን አጠናክራ እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል። ጉባዔውን ለማስተናገድ ኢትዮጵያ ያቀረበችው ጥያቄ በቀጣይ ሂደቶች ተቀባይነት ያገኛል ተብሎ ይጠበቃል።
በአዋሽ ወንዝ ከልማት ውጪ የነበረን ከ70 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ወደ ልማት ማስገባት ተችሏል
Nov 10, 2025 345
አዳማ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ)፦ በአዋሽ ወንዝ ከልማት ውጪ የነበረን ከ70ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ወደ ልማት ማስገባት መቻሉን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) ገለፁ። በአዋሽ ተፋሰስ የጎርፍ አደጋ ስጋትን በዘላቂነት ለማስቀረት የተከናወኑ ተግባራት የአዋጭነት ጥናት ግኝት ላይ ያተኮረ የባለድርሻ አካላት የምክክር መድረክ በአዳማ ከተማ እየተካሄደ ነው።   የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለፁት በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ባሉ ተፋሰሶች የጎርፍ አደጋ ተጋላጭነትና የአፈር መሸርሸርን ለመቀነስ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። በስምጥ ሸለቆና ኦሞ ተፋሰሶች የጎርፍ አደጋ ስጋት ተጋላጭነትን ለመቀነስ በርካታ ሥራዎች እየተከናወኑ ናቸው ብለዋል። በተለይም ባለፉት ሁለትና ሦስት ዓመታት በመካከለኛውና ታችኛው አዋሽ ተፋሰስ ላይ ከ250 ኪሎ ሜትር በላይ በወንዝ ግራና ቀኝ የውሃ መገደቢያ በመስራት የጎርፍ አደጋን የመከላከል ሥራ መከናወኑን አንስተዋል። በዚህም ወንዙ ሲሞላ መገደቢያውን አልፎ በመውጣት አደጋ ሲያደርስ የነበረውን ጎርፍ በመከላከል 70ሺህ 140 ሄክታር መሬት ወደ ልማት እንዲገባ መደረጉን ገልጸዋል። በዚህም ከ129 ሺህ በላይ የሚሆን የህብረተሰብ ክፍልን ከመፈናቀል አደጋ መታደግ ተችሏል ብለዋል።   የአዋጭነት ጥናቱ ዓላማ የአዋሽ ወንዝን በዘላቂነት ከስጋት ነፃ በማድረግ ሙሉ በሙሉ ወደ ልማት ለማስገባትና ወንዙን በሚፈለገው መልኩ ጥቅም ላይ ለማዋል እንዲቻል ያለመ መሆኑንም ተናግረዋል። በወንዙ ግራና ቀኝ በተሰራው የጎርፍ መከላከል ሥራ የማህበረሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ከማረጋገጥ ባለፈ የአደጋ ስጋትና ተጋላጭነትን መቀነስ መቻሉን ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ የሚካሄደው አህጉራዊ የመሬት ፖሊሲ ጉባኤ
Nov 10, 2025 168
አዲስ አበባ፤ ህዳር 1/2018(ኢዜአ):- ስድስተኛው የአፍሪካ የመሬት ፖሊሲ ኮንፍረንስ ከዛሬ ጀምሮ በአዲስ አበባ ይካሄዳል። “የመሬት አስተዳደር፣ ፍትህ እና ካሳ ለአፍሪካውያንና ለዘርዓ አፍሪካውያን” በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የሚካሄደው ኮንፍረንስ መሪ ሀሳብ ነው። የአፍሪካ ህብረት፣ የአፍሪካ ልማት ባንክ እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ኢሲኤ) ኮንፍረንሱን በጋራ አዘጋጅተውታል። ከአፍሪካ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ታሪካዊ እና የአካባቢ ጉዳዮች ጋር የተጣጣሙና ለነባራዊ እውነታዎች ምላሽ የሚሰጡ የመሬት ፖሊሲ ምርጥ ተሞክሮዎች በኮንፍረንሱ ይቀርባሉ። ውጤታማ እና ተጠያቂነት የሰፈነበት የመሬት አስተዳደር ስርዓት መገንባት፣ ተቋማዊ አቅምን መፍጠርና ቁጥጥርና ክትትልን ማጠናከር በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ምክክር እንደሚደረግ ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። ባርነት፣ የቅኝ ግዛት ዘመን መሬት የመንጠቅ ተግባርና በዘር ምክንያት መሬት ከማግኘት መገለል በአፍሪካውያንና ትውልደ አፍሪካውያን የመሬት መብቶች፣ ሀብት አጠቃቀምና እኩልነት ላይ ያሳደራቸውን አሉታዊ ተጽእኖዎች ላይ የጋራ ግንዛቤ በመፍጠር ችግሩን በዘላቂነት መፍታት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይቶች ይካሄዳሉ። በመሬት አስተዳደር፣ ፍትህ እና ካሳ ያሉ ውይይቶች ማጠናከር እና ፖሊሲ ተኮር ምላሾችን መስጠት ሌላኛው የኮንፍረንሱ አላማ ነው። የስርዓተ ጾታ እኩልነት፣ የአየር ንብረት ለውጥና ቴክኖሎጂዎችን ከመሬት ፖሊሲ እና አስተዳደር ጋር ማስተሳሰር ትኩረት ተሰጥቶታል። በኮንፍረንሱ የመሬት ፖሊሲ፣ የመሬት ፍትህ፣ የማካካሻ ፍትህ እና የመሬት ባለቤትነትን በተመለከቱ ጉዳዮች ላይ የፖሊሲ፣ የህግ እና ተቋማዊ ምክረ ሀሳቦች ይቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል። በአህጉራዊ ኮንፍረንሱ የአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት፣ የህብረቱ ተቋማትና አደረጃጀቶች ከፍተኛ አመራሮች፣ተመራማሪዎች፣ የፖሊሲ ባለሙያዎች፣ የማህበረሰብ መሪዎች፣ ትውልደ አፍሪካውያንና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ይሳተፋሉ። ኮንፍረንሱ እስከ ህዳር 5 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የአፍሪካ የመሬት ፖሊሲ ኮንፍረንስ በየሁለት ዓመቱ የሚካሄድ ሁነት ነው።
የኮፕ 30 አጀንዳዎች እና የኢትዮጵያ ተሳትፎ
Nov 10, 2025 266
30ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ(ኮፕ 30) ዛሬ ይጀምሯል። “የአየር ንብረት እርምጃ እና ትግበራ” የጉባኤው ዋና መሪ ሀሳብ ነው። ከኮፕ 30 ቁልፍ ግቦች መካከል የሚከተሉት ይገኙበታል:- የኢነርጂ፣ ኢንዱስትሪ እና ትራንስፖርት ስርዓቶችን ሽግግር ማፋጠን። በዚህም የታዳሽ ኃይልን በሶስት እጥፍ መጨመር፣ የኢነርጂ ዓለም አቀፍ ተደራሽነት ማረጋገጥና የበካይ ጋዞችን በጊዜ ሂደት መጠቀም ማቆም መቀነስ ላይ ያተኮሩ ውይይቶች ይካሄዳሉ። ተፈጥሮን፣ ደኖችን፣ ውቅያኖሶችን የብዝሃ ህይወት ሀብቶችን መጠበቅና ወደ ቀደመ ይዞታቸው መመለስ፣ የደን ጭፍጨፋን ማስቆም እና የተጎዱ ስነ ምህዳሮች ዳግም እንዲያገግሙ ማድረግ። ግብርና እና ስርዓተ ምግብን መቀየር፤ ዘላቂ የመሬት አጠቃቀም፣ የማይበገር ስርዓተ ምግብ መገንባትና የምግብና የስነ ምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ። ለከተሞች፣ ለመሰረተ ልማቶችና ለውሃ ስርዓቶች የማይበገር አቅም መገንባት፣ የሰው ኃይልና ማህበራዊ ልማት እንዲሁም ፋይናንስ እና ቴክኖሎጂን ጨምሮ ሌሎች አቅሞችን መጠቀም። የንግድ ማህበረሰቦች፣ ከተሞች፣ ባለሀብቶችና የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማትን ጨምሮ መንግስታዊ ያልሆኑ አካላት በኮፕ 30 የተግባር አጀንዳ አማካኝነት በበጎ ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ የአየር ንብረት ለውጥ እርምጃ እንዲወስዱ ማድረግ ይገኙበታል።   ከተጠቀሱት ግቦች የተለያዩ ውጤቶችም ይጠበቃሉ። የኮፕ 30 የተግባር አጀንዳ የሚያስፈጽም የድርጊት መርሃ ግብር ማዘጋጀት፣ ቃል የተገቡ ጉዳዮች ወደ ተግባር መለወጥና ተግበራዊነቱን የሚቆጣጠሩ ቡድኖች ከጉባኤው በኋላ እንደሚቋቋሙ ይጠበቃል። ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት የፋይናንስ ግብን ማጠናከር ሌላኛው አጀንዳ ሲሆን የበለጸጉ ሀገራት በማደግ ላይ ለሚገኙ ሀገራት ቃል የገቧቸውን የገንዘብ ድጋፎች እንዲሰጡ ጠንካራ ጥሪ ይቀርባል። የአየር ንብረት ለውጥ ፍትህ፣ ፍትሃዊ የኢነርጂ ሽግግር፣ የቴክኖሎጂ ተደራሽነት፣ አቅም ግንባታና ተጋላጭ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያማከለ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስራ የሚጨበጥ ለውጥ ማምጣት የሚጠበቅ ውጤት ነው። መንግስታዊ ያልሆኑ አካላት በአየር ንብረት ለውጥ ስራዎች ላይ ያላቸውን ሚና ማሳደግና የባለድርሻ አካላትን ትብብር ማጠናከር ትኩረት የተሰጠሰው ጉዳይ መሆኑም ተመላክቷል። ለአፍሪካ ኮፕ 30 ለአየር ንብረት ለውጥ ፈተናዋ መፍትሄ የሚያመጡ ውሳኔዎችን የምትጠብቅበት መድረክም ነው። የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ ተደራሽነት ማሳደግና ፍትሃዊነትን ማስፈን፣ ፍትሃዊ የኢነርጂና የቴክኖሎጂ ሽግግርን ማረጋገጥ፣ ተፈጥሯዊ መፍትሄዎች፣ የብዝሃ ህይወት ጥበቃ፣ ኢኖቬሽን፣ የማይበገር አቅምን መገንባትና የዜጎች መብት ጥበቃ ከአፍሪካ አጀንዳዎች መካከል ይጠቀሳሉ። አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ ዝቅተኛ ድርሻ ቢኖራትም ዋነኛ የችግሩ ገፈት ቀማሽ ናት። ተከታታይ ድርቆች፣ ጎርፎችና በረሃማነት አበይት ፈተናዎቿ ናቸው። በዚህ ረገድ ኮፕ 30 ለአፍሪካ በማይበገር አቅም ግንባታ፣ መሰረተ ልማት አቅርቦትና የኢነርጂ ተደራሽነት ላይ የሚያሳልፋቸው ውሳኔዎች ይጠበቃሉ። የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነት ጉዳይ በኮፕ 30 ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው አፍሪካውያን ይሻሉ። ኮፕ 30 ለአፍሪካ የትርክት ሽግግር የምታደርግበት ነው ማለት ይቻላል። አፍሪካ የችግሩ ተጎጂ ነኝ ከማለት ባለፈ ታዳሽ ኢነርጂ፣ የካርቦን ገበያና አረንጓዴ ኢንዱስትሪዎችን ጨምሮ መፍትሄዎችን አፍላቂ አህጉር መሆኗን በግልጽ የምታሳይበትና ለዓለም ድምጿን የምታሰማበትም ነው።   13ኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥና ልማት ጉባኤ ’’በሳይንስ፣ በገንዘብና በፍትሐዊ ሽግግር የአፍሪካን የአየር ንብረት እርምጃ ማንቃት” በሚል መሪ ሃሳብ በነሐሴ ወር 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ መካሄዱ የሚታወስ ነው። በጉባኤው ላይ የተሳተፈው የአፍሪካ የአየር ንብረት ድርድር ቡድን በብራዚል በሚካሄደው ኮፕ-30 የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤ የአፍሪካን ቀዳሚ የልማት አጀንዳዎች የሚያንጸባርቁ የድርድር ሃሳቦችን ለማቅረብ ዝግጅት መደረጉን ገልጿል። በጉባኤው የአፍሪካን የልማት መሻት ያነገቡ የተቀናጁ፣ ወጥነትና ጥራት ያላቸው የድርድር ሀሳቦች ለማቅረብ ዝግጅት እንደተደረገ አመልክቷል። የአፍሪካን የልማት ጸጋዎች የዓለም አቀፍ የመፍትሔ ለማድረግ በአዲስ አስተሳሰብ በመተባበር ላይ የተመሰረተ ተጨባጭ እርምጃ መውሰድ እንደሚያስፈልግ ቡድኑ ገልጿል። አፍሪካ በ2030 የአየር ንብረት ግቦቿን ለማሳካት ከሚያስፈልጋትና ቃል ከተገባው ውስጥ ከ3 እስከ 4 በመቶ የማይበልጥ የፋይናንስ ድጋፍ እየተደረገላት መሆኑን መረጃዎች ያመክታሉ። ተደራዳሪ ቡድኑ በብራዚል ቤሌም ከተማ በሚካሄደው ኮፕ-30 ጉባኤ ላይ የአፍሪካን የፋይናንስ ፍትሐዊ አጀንዳ በአንድ አህጉራዊ ድምጽ ማሰማት እንደሚያስፈልግና ለዚህም ዝግጅት መደረጉን አስታውቋል። ኢትዮጵያ በኮፕ 30 በአፍሪካ የአየር ንብረት ዲፕሎማሲ ውስጥ የመሪነት ሚናዋን ለመወጣት ተዘጋጅታለች። 30ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ(ኮፕ 30) የተገቡ ቃሎች ወደ ተግባር የሚቀየሩበት ወሳኝ ምዕራፍ ሊሆን እንደሚገባም ደጋግማ ገልጻለች። በአረንጓዴ ዐሻራ አማካኝነት በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከልና በመንከባከብ ኢትዮጵያ ማንንም ሳትጠብቅ ተጨባጭ እርምጃ ወስዳለች። አረንጓዴ ዐሻራ የአየር ንብረት ለውጥን ከመከላከል ባለፈ ለምግብ ዋስትና መረጋገጥና ለሀገር እድገት የበኩሉን ሚና እየተወጣ ይገኛል። ኢትዮጵያ ግብርናውን ጨምሮ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ የታገዙ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል እርምጃዎች እየሰወደች ነው። ሁለተኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባኤ “ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፥ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ የአፍሪካን የጋራ ድምጽ የያዘውን የአዲስ አበባ ድንጋጌ በማጽደቅ መጠናቀቁ ይታወሳል። የአየር ንብረት ጉባኤውን በጋራ ያዘጋጁት ኢትዮጵያ እና አፍሪካ ህብረት የጣምራ መግለጫ ማውጣታቸውም አይዘነጋም። በጉባኤው በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ዶላሮች ቃል መገባታቸውንና ታሪካዊው የአዲስ አበባ ድንጋጌ መጽደቁን ገልጾ፥ ይህም የአፍሪካ መሪዎች በዓለም የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ውስጥ ጠንካራ ተሳትፎ ለማድረግ ያላቸውን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ገልጿል። በጉባኤው ላይ ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ህብረት በ“Africa Climate Innovation Compact” እና “African Climate Facility” የተሰኙ ኢኒሼቲቮችን ይፋ ያደረጉ ሲሆን በዚህም ለሀገር በቀል የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄዎች 50 ቢሊዮን ዶላር ሀብት በየዓመቱ የማሰባሰብ ስራ እንደሚከናወን ተመላክቷል። መሪዎቹ በጉባኤው ላይ የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ፈንድ ወደ ስራ ማስገባት የሚያስችል ስምምነት መፈራረማቸውን የገለጸው የጋራ መግለጫው፥ ፈንዱ እዳን ከሚያሸክሙ ብድሮች ይልቅ የፋይናንስ ድጋፍ ላይ ያተኮረ እንደሆነ ጠቁሟል። በጉባኤው ዓለም አቀፍ አጋሮች የፋይናንስ ድጋፎችን ለማድረግ ቃል ገብተዋል። የአፍሪካ ልማት ባንክ፣ የአፍሪካ ኢምፖርት እና ኤክስፖርት ባንክ(አፍሪኤግዚም ባንክ)፣ አፍሪካ 50 የተሰኘ የመሰረተ ልማት ኢንቨስትመንት ማዕቀፍን ጨምሮ ሌሎች ግዙፍ የፋይናንስ ተቋማት ለአፍሪካ አረንጓዴ ኢንዱስትሪ ኢኒሼቲቭ 100 ቢሊዮን ዶላር ለመስጠት ቃል ገብተዋል። ሌሎች ሀገር በቀል የአየር ንብረት ፕሮጀክቶችን የሚደግፉ አዳዲስ ፕሮጀክቶችም ይፋ ሆነዋል። መሪዎች በጉባኤው አፍሪካ እ.አ.አ በ2030 በዓለም የታዳሽ ኢነርጂ ኢንቨስትመንት ያላትን ድርሻ ከ2 በመቶ ወደ 20 በመቶ ከፍ ለማድረግም ቃል ገብተዋል። የአረንጓዴ ማዕድናት እና ንጹህ የኢነርጂ ተደራሽነት የሚያሰፉ ስትራቴጂዎችን ማጠናከር ሌላኛው ጉባኤው ከስምመነት ላይ የደረሰበት አጀንዳ ነው። አፍሪካ በብራዚል ቤለም የሚካሄደውን (ኮፕ 30) የፀደቀውን የአዲስ አበባ ድንጋጌ አፍሪካ በዓለም የአየር ንብረት ያላትን የመሪነት ሚና የሚያጸና መሆኑን መግለጫው አመልክቷል። ኮፕ 30 ከዓለም የአየር ንብረት አስተዳደር አንጻር ትልቅ ትርጉም ያለው ሲሆን ቃል ኪዳኖቹ ወደ ተጨበጡ ውጤቶችና የተግባር እርምጃዎች የሚቀየሩበት ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል። በጉባኤው የተገቡ ቃሎችና ትግበራን የሚያስታርቅ ነው ያሉትም አልጠፉም። በአጠቃላይ ጉባኤው ሁሉን አካታችና ተግባር ተኮር የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄዎች ከመቼውም ጊዜ በበለጠ የሚስተጋባበትና አስቸኳይ ጥሪ የሚቀርበበት ነው። አፍሪካም በጋራ ድምጿን ከማሰማት ባለፈ ፍትህና የተግባር ምላሽን የምትጠብቅበት ነው። ቃልን ወደ ተግባር መለወጥ የሚጨበጥ ለውጥ በማምጣት መጻኢ ጊዜ ፍትሃዊ እና ዘላቂነትን ላይ የተመረኮዘ እንዲሆን ያስችላል። 30ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ(ኮፕ 30) እስከ ህዳር 12 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል።
72 የአጥቢ እንስሣት ዝርያዎች መገኛ ኦሞ ብሔራዊ ፓርክ
Nov 9, 2025 229
ኦሞ ብሔራዊ ፓርክ ውድምቢ የተሰኘው የዱር እንስሣ ኢትዮጵያ ውስጥ በብቸኝነት መገኛ እንደሆነም ይነገራል። ማራኪ ዕይታና ድንቅ የተፈጥሮ አቀማመጥ የተቸረው ኦሞ ብሔራዊ ፓርክ ዙሪያ-ገባውን ሙርሲ፣ ቦዲ፣ ባጫ፣ ሙጉጂ፣ ኛንጋቶም፣ ሱርማ፣ ዲዚና ሚኒት ብሔረሰቦች አጅበውታል። ፓርኩ በ1959 ዓ.ም. ሲመሠረት 4 ሺህ 68 ስኩየር ኪሎ ሜትር ስፋት እንደነበረው የኦሞ ብሔራዊ ፓርክ ዋና ኃላፊ ኑሩ ይመር ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ተናግረዋል። ይህ አሃዝ በ2012/13 ዳግም በተደረገ የመከለል ሥራ ወደ 5 ሺህ 149 ስኩየር ኪሎ ሜትር ከፍ ማለቱንም ጠቅሰዋል።   72 የአጥቢ እንስሣት ዝርያዎች በፓርኩ ውስጥ እንደሚኖሩ የጥናት ውጤቶች ማመላከታቸውን ጠቅሰዋል። ከእነዚህ መካከልም አምሥቱ ትላልቅ የአፍሪካ አጥቢ እንስሣት መሆናቸውን ጠቁመው፤ እነሱም ዝሆን፣ አንበሳ፣ ነብር፣ አውራሪስና ጎሽ እንደሆኑ አብራርተዋል። በተጨማሪም ከ325 በላይ የአዕዋፍ፣ ከ24 በላይ የተሳቢና ተራማጅ፣ ከ13 በላይ የዓሣ ዝርያዎች እንደሚገኙ አስረድተዋል። እንዲሁም ፓርኩ ከ600 በላይ የእፅዋት ዝርያዎች መገኛ መሆኑን ነው የተናገሩት። ብሔራዊ ፓርኩን ከተለያዩ ሕገ ወጥ ተግባራት ለመጠበቅ ከአካባቢው ነዋሪዎች እና ከመንግሥት መዋቅር ጋር በቅንጅት እየተሠራ መሆኑንም አረጋግጠዋል።
የደን ሀብትን የማልማትና የመጠበቅ ባህልን ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ እየሰራን እንገኛለን-የደን ልማት ማህበር አባላት
Nov 8, 2025 147
ቦንጋ፤ ጥቅምት 29/2018 (ኢዜአ)፦ የቆየውን የደን ሀብት የማልማትና የመጠበቅ ባህልን ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ እየሰሩ እንደሚገኙ በካፋ ዞን የጊምቦ ወረዳ ደን ልማት ማህበር አባላት ገለፁ። የካፋ ዞን የበርካታ ተፈጥሮ ሀብቶች ባለቤት ሲሆን ከነዚህም በዓለም በቅርስነት የተመዘገበው የበርካታ ብርቅዬ ብዝሃ-ህይወት መገኛው የካፋ ባዮስፌር አንዱ ነው። የካፋ ባዮስፌር በውስጡ ጥብቅ ደኖችንና ዘላቂ የልማት ሞዴልን የያዘ ሲሆን የአረቢካ ቡና፣ የበርካታ ሀገር በቀል ዛፎች፣ የመድኃኒት እፅዋት፣ የብርቅዬ እንስሳትና አእዋፋት ዝርያዎች መገኛ ነው።   በዚህ ባዮስፌር ውስጥም አሳታፊ የደን ልማት ማህበራት የሚገኙ ሲሆን ማህበራቱም በዞኑ የደን ሀብትን የማልማትና የመጠበቅ ባህልን ለቀጣይ ትውልድ ለማስተላለፍ እየሰሩ መሆናቸውን ይገልፃሉ። በጊምቦ ወረዳ ሚቺቲ ቀበሌ ውስጥ ከሚገኙ የደን ማህበራት መካከል የበካ ደን ልማት ማህበር ሰብሳቢ አቶ መብራቱ ገብረመስቀል ከአያቶቻቸው የተረከቡትን ደን የመጠበቅ ባህልን ማስቀጠላቸውን ጠቅሰው ማህበራቸው 130 አባላትን ይዞ ከ600 ሄክታር በላይ መሬት የሸፈነውን ስፍራ እየጠበቁ መሆናቸውን ተናግረዋል።   ከጥበቃው ጎን ለጎንም በክፍት ቦታዎች ላይ አዳዲስ ችግኞችን በመትከል የአካባቢው ስነ ምህዳር እንደተጠበቀ እንዲቆይ እየሰሩ መሆኑንም አክለዋል። በአካባቢው ዘመናዊ የደን አጠባበቅ ስርዓት እንዲኖር ተደራጅቶ መንቀሳቀሱ ዘላቂ ልማትና ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ሚናው የጎላ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የማህበሩ አባል አቶ ገረመው አሰፋ ናቸው።   ማህበሩ በስሩ ባሉት ስድስት ሳይቶች የተለያዩ ኮሚቴዎችን በማዋቀርና የችግኝ ጣቢያዎችን በማቋቋም በየዓመቱ ተጨማሪ ችግኞችን በመትከል የደን መጠኑ እንዲጨምር እያደረገ መሆኑንም ገልፀዋል። የካፋ ዞን ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ህብረት ስራ ልማት መምሪያ የተፈጥሮ ሀብት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ታሪኩ ወልደሚካኤል፣ የካፋ ማህበረሰብ በደን አጠባበቅ ላይ የቆየ ልምድ አለው ብለዋል።   ዘመናትን የተሻገረው የካፋ ማህበረሰብ የደን አጠባበቅ ባህል አሁንም ተጠናክሮ መቀጠሉን ጠቅሰው ይህም በርካታ ትሩፋቶችን እያስገኘ ስለመሆኑም አስረድተዋል። በዚህም በዞኑ 66 ሺህ 500 ወንድና ሴት አባላት ያላቸው 265 ማህበራት ተደራጅተው ከ218 ሺህ 195 በላይ ሄክታር ደን በመጠበቅ ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል። የካፋ ባዮስፌር የአረቢካ ቡና መገኛ ብቻም ሳይሆን ከአምስት ሺህ በላይ የቡና ዘረመሎች፣ ሀገር በቀል የዛፍ ዝርያዎች እንዲሁም የተለያዩ አእዋፋት፤ ብርቅዬ የአንበሳ ዝርያና ሌሎች እንደሚገኙበትም ገልፀዋል። በዓለም ቅርስነት የተመዘገበው የካፋ ባዮስፌር 760 ሺህ ሄክታር መሬትን የሚሸፍን ሲሆን ከዚህም ውስጥ 52 በመቶው ጥብቅ ደን መሆኑን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ይጠቁማል።
በጋምቤላ ክልል በባዮስፌር ሪዘርቭ የተመዘገቡ ደኖችን ለዘላቂ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ለማዋል ትኩረት ተደርጓል
Nov 8, 2025 138
ጋምቤላ፤ጥቅምት 29/ 2018 (ኢዜአ)፦በጋምቤላ ክልል በባዮስፌር ሪዘርቭ የተመዘገቡ ደኖችን ለዘላቂ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ለማዋል በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ አካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ቢሮ አስታወቀ። የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ በበኩሉ በክልሉ በባዮስፌር ሪዘርቭ የተመዘገቡ የተፈጥሮ ደን ሀብቶችን በመጠበቅ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳውን ለማጉላት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የክልሉ አካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሯች ባየክ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከልና ብዝሃ ህይወት መጠበቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል።   የጋምቤላ ክልልም ባከናወናቸው የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች የማጃንግና የአኝዋሃ ዞኖች የተፈጥሮ ደኖች በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት /ዩኔስኮ/ በባዮስፌር ሪዘርቭ መመዝገባቸውን በማሳያነት ጠቅሰዋል። በክልሉ በባዮስፌር ሪዘርቭ የተመዘገቡ ደኖች በውስጣቸው በርካታ የእንስሳት፣ የዕጽዋትና የውሃ አካላትን የያዙ መሆናቸውን ጠቁመዋል። እነዚህ ሀብቶችን በመጠበቅና በመንከባከብ ለዘላቂ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ለማዋል በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በዩኔስኮ በባዮስፌር ሪዘርቭ የተመዘገቡት የተፈጥሮ ደኖች የአየር ንብረት ሚዛንን በማስጠበቅ ለዘላቂ የግብርና ልማት የጎላ ሚና እንዳላቸው ተናግረዋል። የተፈጥሮ ደን ሀብቶቹ ብዝሃ ህይወትን መያዛቸው በዘርፉ ለሚደረጉ ጥናትና ምርምር ስራዎች ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥሩም ገልጸዋል። የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ኮንግ ኛክ በበኩላቸው፥ እንደ ሀገር በዩኔስኮ እውቅና አግኝተው በባዮስፌር ሪዘርቭ ከተመዘገቡት ስድስት የተፈጥሮ ደኖች መካከል ሁለቱ በጋምቤላ ክልል እንደሚገኙ ተናግረዋል።   በመሆኑም የተፈጥሮ ደኖች በዓለም አቀፍ ደረጃ በባዮስፌር ሪዘርቭነት ያገኙትን እውቅናና በውስጣቸው የሚገኙ የብዝሃ ህይወት ሃብቶችን በማስተዋወቅ ለቱሪዝም ልማት ለማዋል እየተየሰራ ነው ብለዋል። ቢሮው ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት በደን ሀብቶች ላይ ተጨማሪ የጥናት ስራዎችን በመስራት የዘርፉን ጥቅም የማሳደግና የቱሪስት መዳረሻዎችን የማልማት ስራ እንደሚከናወንም አመልክተዋል።
የአፍሪካ ጥያቄ ምጽዋት አይደለም የምንፈልገው የአየር ንብረት ፍትህ እና ፍትሃዊ የፋይናንስ አቅርቦት ነው - መሐሙድ አሊ ዩሱፍ
Nov 8, 2025 169
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 29/2018(ኢዜአ)፦ አፍሪካ ምጽዋት አትፈልግም ጥያቄያችን የአየር ንብረት ፍትህ እና ፍትሃዊ የፋይናንስ አቅርቦት ሊኖር ይገባል የሚል ነው ሲሉ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። ለአየር ንብረት ለውጥ ዝቅተኛ ድርሻ ያላቸው የአፍሪካ ሀገራት ከፍተኛውን የጉዳት ቀንበር ሊሸከሙ አይገባምም ብለዋል። 30ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 30) ከህዳር 1 እስከ 12 ቀን 2018 ዓ.ም በብራዚል ቤለም ይካሄዳል። “የአየር ንብረት እርምጃ እና ትግበራ” የጉባኤው ዋና መሪ ሀሳብ ነው። ከዋናው ጉባኤ በፊት የቤለም የአየር ንብረት የመሪዎች ጉባኤ ተካሂዷል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር አፍሪካ ወደ ኮፕ 30 ጉባኤ በጠንካራ አቋም መምጣቷን ገልጸው አህጉሪቷ የለውጥ ወኪል ናት ሲሉ ተናግረዋል። ከፀሐይ ኃይል ማመንጫ ስፍራዎች እስከ አረንጓዴ ኢንቬሽን ባለቤት ወጣቶች የያዘችው አፍሪካ ቀጣዩ ጊዜ ፍትሃዊ፣ ሁሉን አቀፍ እና ዝቅተኛ የካርቦን ልህቀት እንዲሆን የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች እንደምትገኝ ገልጸዋል። አፍሪካ የዓለም 40 በመቶ የታዳሽ ኃይል አቅም ያላት ቢሆንም የምታገኘው የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ ከ12 በመቶ በታች መሆኑን አመልክተዋል። እኛ የጠየቅነው በጎ አድራጎት አይደለም ያሉት ሊቀ መንበሩ የምንፈልገው የአየር ንብረት ፍትህ፣ ፍትሃዊ የፋይናንስ፣ ቴክኖሎጂ እና እድሎች ተደራሽነት ነው ብለዋል። ለአየር ንብረት ለውጥ ውስጥ ዝቅተኛ አስተዋጽኦ የሚያበረክቱ ሀገራት ከፍተኛውን ቀንበር መሸከም የለባቸውም ነው ያሉት። ኮፕ 30 ዓለም ከቃል መግባት ወደ ለውጥ፣ ከተጋላጭነት ወደ ጥንካሬ መሸጋገር እንዳለበት ገልጸው የአየር ንብረት ለውጥን የመከላከል ስራ በአጋርነት፣ በፍትሃዊነት እና የጋራ ብልጽግና እሳቤዎች ሊመራ እንደሚገባውም አመልክተዋል። ግማሽ መፍትሄ ብቻ የሚያመጡ እርምጃዎችን የመውሰድ ጊዜ አብቅቷል፤ አሁን የሚያስፈልገው ድፍረት የሞላበት እና የጋራ የተግባር ምላሽ ነው ማለታቸውን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በበጋ ወራት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት ሥራ ለማከናወን ዝግጅት ተደርጓል
Nov 7, 2025 150
ጎንደር፤ ጥቅምት 28/2018 (ኢዜአ):-በማዕከላዊ ጎንደር ዞን በዘንድሮ የበጋ ወራት በ879 ነባርና አዲዲስ ተፋሰሶች ላይ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና ልማት ሥራ ለማከናወን የሚያስችል ዝግጅት መደረጉን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ፡፡ የተፈጥሮ ሀብት የንቅናቄ መድረክ ዛሬ በጎንደር ከተማ ተካሂዷል፡፡   የመምሪያው ሃላፊ አቶ ንጉሴ ማለደ እንደገለጹት፤ ባላፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የልማት ሥራዎች የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት በማሳደግ ተጨባጭ ለውጥ አምጥተዋል፡፡ ባገገሙ ተፋሰሶች ላይ አርሶ አደሩን በንብ ማነብ፣ በእንስሳት ማድለብ፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ልማትና በሌሎች የልማት ሥራዎች በማሳተፍ የተሻለ ገቢ እንዲያገኝ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ተናግረዋል፡፡ በቅድመ ዝግጅት ወቅት በዞኑ በተለያዩ ወረዳዎች ከ473 ሺህ በላይ ተሳታፊ አርሶ አደሮችን በ3ሺህ 66 የልማት ቡድኖች የማደራጀት ሥራ መከናወኑንም አስረድተዋል፡፡ ከ41ሺህ ሄክታር በላይ የተራቆቱ መሬቶች ላይ የእርከንና ክትር ሥራዎችን ጨምሮ የውሃ ስርገትን የሚጨምሩ የልማት ሥራዎች እንደሚከናወኑ ተናግረዋል። የተፈጥሮ ሀብት ልማት ሥራ የሚከናወንባቸውን ተፋሰሶች በመጪው የክረምት ወራት በስነ ህይወታዊ ዘዴ ለማጠናከርም ከ141 ሚሊዮን በላይ ሀገር በቀል ችግኞች የማፍላት ሥራ ይከናወናል ብለዋል፡፡   ባለፉት አምስት ዓመታት በተከናወነው የችግኝ ተከላና ክብካቤ ሥራ የዞኑን የደን ሽፋን በአሁኑ ወቅት 14 ነጥብ 5 በመቶ ለማድረስ መቻሉን አስረድተዋል፡፡ የዞኑ አርሶ አደሮች በለሙ አካባቢዎች ኢኮኖሚያዊ ጥቅም በማግኘታቸው ለተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ ልዩ ትኩረት እየሰጡ መጥተዋል ያሉት ደግሞ የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ ተወካይ አቶ ክንዱ ዘውዱ ናቸው፡፡   በዞኑ የተቋቋሙ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ጽህፈት ቤቶች የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥና ያገገሙ ተፋሰሶች ዘላቂነታቸው እንዲጠበቅ ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። የላይ አርማጭሆ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አስረሳው ደሴ በበኩላቸው እንዳሉት ወረዳቸው በተፈጥሮ ሀብት ልማት ሥራ ሞዴል ከሚባሉ ወረዳዎች የሚጠቀስ ነው። አርሶ አደሮችም በለሙ ተፋሰሶች ላይ በንብ ማነብና በፍራፍሬ ልማት በመሰማራት የተሻለ ገቢ በማግኘት ኑሮዋቸውን እየለወጡ መምጣታቸውን አስረድተዋል።
የባሌ ህዝብ ከገዳ ሥርዓት በወረሰው አስተምህሮ እና ዕሴት የተፈጥሮ ሃብቶችን በመጠበቅ አብሮ መኖርን ባህሉ ያደረገ ህዝብ ነው
Nov 5, 2025 311
ሮቤ ፤ጥቅምት 26/2018(ኢዜአ)፦ የባሌ ህዝብ ከገዳ ሥርዓት በወረሰው አስተምህሮ እና ዕሴት የተፈጥሮ ኃብቶችን በመጠበቅ አብሮ መኖርን ባህሉ ያደረገ ህዝብ ነው ሲሉ የአካባቢው የሃገር ሽማግሌዎች እና ምሁራን ተናገሩ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የሥራ ዘመን ሁለተኛ መደበኛ ስብሰባ ላይ ካነሱዋቸው ሀሳቦች መካከል የባሌ ህዝብ ከተፈጥሮ ሀብት ጋር ያለው መስተጋብር አንዱ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ፣ “የባሌ ሕዝብ አመቺ ባልሆነ ሁኔታ ውስጥ ሆኖ የጋራ የተፈጥሮ ሀብቶችን ጠብቆ በማቆየቱ ሊመሰገን ይገባል” ብለው ነበር። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለዞኑ ህዝብ ያቀረቡት ምስጋናና አክብሮት የተፈጥሮ ጸጋዎችን በመንከባከብ ይበልጥ አልምቶ ለመጠቀም የሚያነሳሳ መሆኑን ኢዜአ ያነጋገራቸው የሃገር ሽማግሌዎች እና ምሁራን ገልጸዋል፡፡ ከሮቤ ከተማ የሀገር ሽማግሌዎች መካከል አቶ ተማም ጀማል፣ በተፈጥሮ ጸጋዎች የታደለው የባሌ ዞን የበርካታ ብዝሀ ህይወት ባለቤት እንደሆነ ገልጸዋል፡፡   የቱሪዝም መዳረሻ የሆነው የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ፣ የሐረና ጥብቅ ደንና ሌሎች ውብና ማራኪ መልካም ገጽታን የተላበሰ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ እንዳለው ጠቅሰው ፓርኩ የተለያዩ ብርቅዬ የዱር እንስሳትና አዕዋፋት መገኛ እንደሆነም አንስተዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለፓርኩ ልማትና ብዝሀ ህይወት ጥበቃ የሰጡት ትኩረት ብሎም ለዞኑ ህዝብ ያቀረቡት ክብርና ምስጋና በታሪክ የሚታወስና ለዘላቂ ጥበቃ የሚያነሳሳ ነው ብለዋል፡፡ በተለይ ለዘመናት ሳይለማ የተረሳው የሶፍ ኡመር ዋሻ የኢትዮጵያን ታላቅነትና መልካም ገጽታ ለአለም ህዝብ ጭምር የሚያስተዋውቅ ሌላ ቅርስ መሆኑን የገለጹት ደግሞ አቶ አማን ሐጂ አብዶ ናቸው።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለዞኑ ህዝብ ያቀረቡት ምስጋናና አክብሮት የተፈጥሮ ጸጋዎችንና የደን ቅሪቶችን ይበልጥ በመንከባከብ አልምቶ ለመጠቀም የሚያነሳሳ እንደሆነም አመልክተዋል። የመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የአካባቢ ሳይንስ ዘርፍ መምህራንም የአገር ሽማግሌዎችን ሀሳብ በመጋራት የጋራ የተፈጥሮ ሀብቶችን በመንከባከብ ለዛሬ ላቆየው የባሌ ህዝብ በመንግስት የቀረበው እውቅናና ክብር ለዘላቂ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ አዎንታዊ አንድምታ እንደሚኖረው ገልጸዋል። በተለይም በጥብቅ ደኖች አካባቢ የሚኖሩ ነዋሪዎች በአሳታፊ የደን ልማት አስተዳደር በመደራጀት ደኑን በመጠበቅ ከስነ-ምህዳሩ ከሚያገኙት ጥቅም በተጓዳኝ ከካርቦን ሽያጭ ተጨማሪ ገቢ እያገኙ መምጣታቸው የጥበቃውን ተግባር ይበልጥ የሚያጠናክር መሆኑንም ተናግረዋል። የዩኒቨርሲቲው የአካባቢ ሳይንስ ዘርፍ መምህርና ተመራማሪ ኡመር አብደላ፣ የባሌ ህዝብ ከገዳ ሥርዓት በወረሰው አስተምህሮትና ዕሴት የተፈጥሮ ኃብቶችን በመጠበቅ አብሮ መኖርን ባህሉ ያደረገ ህዝብ መሆኑን ተናግረዋል ።   በተለይ የአካባቢው የተፈጥሮ ሀብት በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም (ዩኔስኮ) በቋሚ ቅርስነት መመዝገቡን ገልፀው የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክና በውስጡ የሚገኙ የብዝሀ ህይወት ስብጥሮች ማህበረሰቡ ጠብቆ ያቆየው ሃብት መሆኑን አመልክተዋል። የባሌ ህዝብ የተፈጥሮ ኃብቱን በመንከባከብ ለትውልድ በማቆየቱ ከመንግሥት የተሰጠው እውቅና የጥበቃውን ሥራ ይበልጥ ውጤታማና ዘላቂ የሚያደርግ መሆኑን የገለጹት ደግሞ ሌላው የዘርፉ መምህርና ተመራማሪ አብዱልፈታህ አብዱ ናቸው።   የተሰጠው እውቅናም የህዝቡ ብቻ ሳይሆን በዘርፉ ይስተዋሉ በነበሩ ተግዳሮቶች ዙሪያ ጥናት በማካሄድ ምክረ ሀሳብ ሲለግሱ ለቆዩት የዘርፉ ምሁራንን ጭምር የሚያነሳሳ መሆኑን አስታውሰዋል።
የአፍሪካ ሀገራት የብዝሃ ህይወት ጥበቃን የልማት አጀንዳቸው የትኩረት ማዕከል ሊያደርጉ ይገባል- ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ 
Nov 4, 2025 297
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 25/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሀገራት የብዝሃ ህይወት ጥበቃና እንክብካቤን እንደ ልማት አጀንዳ በመያዝ መስራት እንደሚገባቸው የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ ገለጹ። የመጀመሪያው የአፍሪካ የብዝሃ ህይወት ጉባኤ በቦትስዋና ጋቦሮኒ ከጥቅምት 23 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ እየተካሄደ ይገኛል። ጉባኤው ላለፉት ሁለት ቀናት በባለሙያዎች ደረጃ ሲከናወን ቆይቶ ዛሬ በሚኒስትሮች ደረጃ ተካሂዷል።   “የብዝሃ ህይወትን በዘላቂነት በመጠቀም የአፍሪካን ብልጽግና ማረጋገጥ” በመሪ መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ያለው ጉባኤ በአፍሪካ ብዝሃ ህይወት ሀብቶች፣ እድሎች፣ ፈተናዎችና ቀጣይ እርምጃዎች የሚመክር ነው። የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ በስብሰባው ላይ ባደረጉት ንግግር የአፍሪካ የተፈጥሮ ሀብት ከጸጋ ባሻገር የአህጉሪቱ የኢኮኖሚ እድገት፣ የምግብ ዋስትና እና የባህል ማንነት መሰረት መሆኑን አመልክተዋል። ብዝሃ ህይወት እና ተፈጥሯዊ ቅርሶች የዓለም ተፈጥሮ ሀብት ዘቦች ሆነው እያገለገሉ እንደሚገኙም ተናግረዋል። ይሁንና የአየር ንብረት ለውጥ፣ የእንስሳትና እጽዋት መኖሪያ ቦታ መውደም እና የተለያዩ ዝርያዎች መጥፋት የብዝሃ ህይወት ሀብቶች አደጋ ላይ እንዲወድቁ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። አፍሪካውያን ብዝሃ ህይወትን የአህጉሪቱ የልማት አጀንዳ ምሰሶ መሆኑን በመገንዘብ አስፈላጊውን ጥበቃ በማድረግ ቁርጠኝነታቸውን ሊያሳዩ ይገባል ነው ያሉት። በአጀንዳ 2063 የበለጸገች እና ሰላማዊ አፍሪካን የመፍጠር ህልም ሊሳካ የሚችለው በዜጎች ትጋትና በዘላቂ አካባቢ ጥበቃና አስተዳደር መሆኑንም አመልክተዋል። አህጉራዊ አጀንዳዎችን ለማሳካት የፖሊሲ ማዕቀፎችን ማጠናከር፣ በተፈጥሮ መፍትሄዎች ላይ መዋዕለ ንዋይን ማፍሰስ እንዲሁም ወጣቶችና ሀገር በቀል ማህበረሰቦችን በብዝሃ ህይወት ጥበቃ የመሪነት ሚና እንዲወጡ ማድረግ እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል። የአፍሪካ ሀገራት ንግግራቸውን ወደ ተጨባጭ ስራ እና ወደሚለካ ውጤት በመቀየርና የአካባቢ ስነ ምህዳርን በመጠበቅ መጻኢውን ጊዜ የተሻለ ለማድረግ እንዲሰሩ አስገንዝበዋል። አፍሪካን በዓለም የብዝሃ ህይወት ጥበቃ እና ዘላቂ አጠቃቀም መሪ እናድርጋት፣ ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለ ነገር እናስረክብ ሲሉም ኮሚሽነሩ ጥሪ አቅርበዋል። በጉባኤው ላይ የአካባቢ ጥበቃ ሚኒስትሮች፣ የዓለም የብዝሃ ህይወት ጥበቃ መሪዎች እና ተመራማሪዎች፣ ሀገር በቀል የማህበረሰብ መሪዎች፣ ባለሀብቶች፣ የግሉ ዘርፍ ተዋንያን፣ የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት፣ ዓለም አቀፍ አጋሮች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል። የመጀመሪያው የአፍሪካ የብዝሃ ህይወት ጉባኤ ነገ በመሪዎች ደረጃ በሚደረግ ስብሰባ ይጠናቀቃል። ጉባኤው ለአፍሪካ ብዝሃ ህይወት መመናመን፣ የአየር ንብረት ለውጥ እና ብክለት የተቀናጀ አህጉራዊ ምላሽ መስጠት የሚያስችል መድረክ መሆኑን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ የስነ-ምህዳር እና ብዝኃ-ሕይወት ጥበቃ ስራዎች ለሌሎች ሀገራት ምሳሌ የሚሆኑ ናቸው
Nov 4, 2025 277
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 25/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በስነ-ምህዳር እና ብዝኃ-ሕይወት ጥበቃ የምታከናውናቸው ተግባራት ከቀጣናው ባሻገር ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ምሳሌ መሆናቸውን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም የስነ-ምህዳርና ባዮ-ዳይቨርሲቲ ዋና የቴክኒክ አማካሪ ዶለይ ጸሪንግ ገለጹ፡፡ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም የስነ-ምህዳርና ባዮ-ዳይቨርሲቲ ዋና የቴክኒክ አማካሪ ዶለይ ጸሪንግ ኢትዮጵያ በልዩ ልዩ ስነ-ምህዳርና ብዝሃ ህይወት የታደለች ሀገር ናት ብለዋል፡፡ የብዝሃ ህይወት እና ስነ-ምህዳር ጥበቃ ለዘላቂ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ልማት ወሳኝ ሚና እንደሚያበረክት ጠቁመው፤ ተቋማቸው በአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከበርካታ የዓለም ሀገራት ጋር በቅንጅት እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያ በብሔራዊ ፓርኮች ጥበቃን በማጠናከር እና አዳዲስ ስፍራዎችን በማልማት ለብዙ አይነት የዱር እንስሳትና ዕፅዋት ወሳኝ መኖሪያ እያለማች መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በትላልቅ የደን ልማት እያከናወነች ያለው ተግባር ከአፍሪካ ቀንድ አልፎ በዓለም አቀፉ ደረጃ ግንባር ቀደም እንደሚያደርጋት ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ በስነ-ምህዳር እና ብዝሃ ህይወት ጥበቃ ዘርፍ እያከናወነች ያለው ተግባር አስደናቂ መሆኑን አመላክተዋል፡፡ የብዝሃ ህይወት ጥበቃ ስራዎች ቀጣዩን ትውልድ ጭምር ታሳቢ ያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡   በተለይ ደግሞ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ከአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እና ከብዝኃ-ሕይወት ጥበቃ ጋር ለማስተሳሰር እየወሰደቻቸው ያሉ እርምጃዎች የሚደነቁ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ ኢትዮጵያ በስነ-ምህዳር እና ብዝኃ-ሕይወት ጥበቃ ረገድ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት ከቀጣናው ባሻገር ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ምሳሌ የሚሆኑ ናቸው ብለዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም ኢትዮጵያ የምታከናውነውን የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራን እንደሚያግዝም አረጋግጠዋል፡፡ የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም በቀጣናው የሚገኙትን ሥነ-ምህዳሮችና የብዝሃ ሕይወትን ለመጠበቅ ከመንግሥት፣ ከሲቪል ማኅበራት እና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡   በኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን ከፍተኛ ተመራማሪ (ዶ/ር) ፋኑዔል ከበደ በበኩላቸው፤ የዱር እንስሳት ለቱሪዝም መስህብነትና ለሌሎችም ጉልህ ድርሻ እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም ኢትዮጵያ የእነዚህን እንስሳት መኖሪያ የመጠበቅ ስራን በትኩረት እየሰራች መሆኑን ጠቁመው በዚህም አበረታች ውጤት እየተመዘገበ እንደሚገኝ አመላክተዋል፡፡ በዚህም በርካታ የዱር እንስሳት አሁን ላይ ወደ ነባር ቀዬያቸው እየተመለሱ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
በመካከለኛው፣ምስራቅ እና የደቡባዊ ደጋማ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ የሌሊቱና የማለዳው ቅዝቃዜ እየጨመረ ይሄዳል
Nov 3, 2025 306
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 24/2018(ኢዜአ)፦በመካከለኛው፣ምስራቅ እና የደቡባዊ ደጋማ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ የሌሊቱና የማለዳው ቅዝቃዜ ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ እንደሚሄድ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው በመካከለኛው፣ምስራቅ እና የደቡባዊ ደጋማ የሀገሪቱ አካባቢዎች የአየሩ ሁኔታ እንደሚቀያየር አስታውቋል። በደብረ ብርሃን፣አርሲ ሮቤ፣አዳባ፣ደሴ፣ባሌ ሮቤ፣አዲስ አበባ፣አደሌ፣አምባ ማሪያም፣ ኮምቦልቻ፣ አንኮበር በአብዛኛው ቀናቶች ላይ ከአምስት ዲግሪ ሴልሺየስ በታች እንደሚሆን የትንበያ መረጃዎች እንደሚያሳዩ ገልጿል። የበጋ ወቅት ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው የሆኑት የደቡብ፣ደቡብ ምዕራብና ደቡብ ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች በሚቀጥሉት አስር ቀናት ዝናብ ያገኛሉ ተብሏል። በሌላ በኩል አብዛኛው የሀገሪቱ ክፍሎች ላይ የበጋው ደረቅ፣ጸሐያማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ ተጠናክሮ ይቀጥላል። በመካከለኛው፣የምስራቅ እና ደቡብ ደጋማ ቦታዎች ላይ የሌሊቱና የማለዳው ቅዝቃዜ ከቀን ወደ ቀን እየጨመረ እንደሚሄድ የሚቲዎሮሎጂ መረጃዎች እንደሚያሳዩ ገልጿል። በሚቀጥሉት አስር ቀናት ዝናብ ሰጭ የአየር ሁኔታ ክስተቶች በጋ ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብሏል። ደቡብ ምዕራብ፣ ደቡብ እና ደቡብ ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ ይኖራቸዋል። የመኽር ሰብል አብቃይ በሆኑት የደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች በወሩ ያለው እርጥበት ዘግይተው ለተዘሩት፣ የእድገት ጊዜያቸውን ላልጨረሱ ሰብሎች፣ለቋሚ ተክሎችና ፍራፍሬዎች የውሃ ፍላጎት ለማሟላት ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥር ገልጿል። ያለው እርጥበት ለእንስሳት መኖም አዎንታዊ አበርክቶ እንዳለው ጠቁሟል። በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበጋ እርጥበት ተጠቃሚ ተፋሰሶች ላይ የተሻለ የገጸ ምድር የውሃ ፍሰት እንደሚኖራቸው የሚጠበቅ ሲሆን የተቀሩት ተፋሰሶች ዝቅተኛ እርጥበት እንደሚኖራቸው ትንበያው ያሳያል ብሏል። አብዛኛው የባሮ አኮቦ፣ኦሞ ጊቤ፣ገናሌ ዳዋ፣ኦጋዴን፣ በመካከለኛው እና በታችኛው ስምጥ ሸለቆ፣ዋቤ ሸበሌ የተሻለ የገጸ ምድር ውሃ ፍሰት እንደሚኖራቸው ጠቁሟል። አብዛኛው አፋር ደናክል፣አዋሽ፣ተከዜ፣መረብ ጋሽ እንዲሁም አይሻ ተፋሰሶች ላይ ደረቅ የአየር ሁኔታ ጠባይ ተጽዕኖ ስር እንደሚወድቁ የአየር ትንበያ ያሳያል ብሏል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም