አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከ902 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ተለይቶ ለችግኝ መትከያ ዝግጁ ተደርጓል - የኢትዮጵያ ደን ልማት
Jun 3, 2023 69
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ)፡- ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከ902 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ተለይቶ ለችግኝ መትከያ ዝግጁ መደረጉን የኢትዮጵያ ደን ልማት ገለጸ፡፡ ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ ሀሳብ አመንጪነት ከአራት ዓመት በፊት በጀመረችው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከ25 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን መትከል ችላለች፡፡ የሀገሪቱን ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ፣ የዜጎችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥና የደን ሽፋኑን በማሳደግ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ታላሚ ባደረገው በዚህ መርሐ ግብር ከተተከለው አጠቃላይ ችግኝ 55 በመቶ የሚሆነው ለጥምር ደን መሆኑ ይታወቃል፡፡ የኢትዮጵያ ደን ልማት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሞቱማ ቶሌራ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ባለፉት አራት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የተከናወነው ሁሉን አቀፍ እንቅስቃሴ እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሁሉ በስኬቱና ህዝባዊ ተሳትፎን በማረጋገጥ የሚጠቀስ ፕሮጀክት ነው፡፡ "በኢትዮጵያ በየዓመቱ በብዙ ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ችግኞች ካልተተከሉ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ለከፋ አደጋ የምንጋለጥበት ዘመን በመሆኑ ለኢትዮጵያውያን ችግኝ መትከል የምርጫ ጉዳይ አይደለም" ብለዋል ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፡፡ በኢትዮጵያ ተራራማ አካባቢዎች እየተራቆቱ፤ አፈር እየተሸረሸረ፤ የውኃማ አካላት እየደረቁ፤ መምጣታቸውን ጥናቶች እንደሚያሳዩ ጠቁመው፤ አረንጓዴ አሻራ ቅድሚያ የሚሰጠው ስራ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከ6 ነጥብ 5 ቢሊዮን በላይ ችግኝ ለመትከል ዕቅድ ቢያዝም እስካሁን ከ7 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ ተናግረዋል። ለዚህ ደግሞ ምን አይነት ችግኞች በምን አይነት ሥነ ምህዳርና በምን አይነት አፈር ላይ ይተከሉ የሚለው በጥናት ተለይቶ ለተከላ ዝግጅት መደረጉን በማብራራት፡፡ በዚሁ መሰረት እስካሁን ከ902 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ተለይቶ ለችግኝ መትከያ የተዘጋጀ ሲሆን ከዚህ ውስጥ 522 ሺህ ሄክታር የሚሆነው ለደን መለየቱን ጠቁመዋል፡፡ ለችግኝ መትከያ ከተለየው መሬት ውስጥ 257 ሺህ ሄክታር የሚሆነው ካርታ እንደተዘጋጀለት ነው የገለጹት፡፡ በመጀመሪያው ምዕራፍ በተካሄዱት አራት የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብሮች ከዘር መረጣ ጀምሮ በችግኝ ተከላና በእንክብካቤ የህብረተሰቡ ተሳትፎ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ መምጣቱን አረጋግጠናል ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካል በሆነው የበጋ ወቅት የተቀናጀ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ የዜጎች ተሳትፎ እየጨመረ መምጣቱ ለዚህ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ ችግኝ መትከል የመርሐ ግብሩ የመጀመሪያ እርምጃ መሆኑን ጠቅሰው፤የተተከሉ ችግኞች ለሚፈለገው አላማ ውለው ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ የመጨረሻ ግቡ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በዘንድሮው መርሐ ግብር እስካሁን ወደ 2 ነጥብ 3 ቢሊዮን የሚጠጋ የችግኝ መትከያ ጉድጓድ መዘጋጀቱን ተናግረዋል። እንደ ዶክተር ሞቶማ ገለጻ፤ በ2015 የበልግ ወቅት በኦሮሚያ፣ ሲዳማ፣ ደቡብ፣ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያና ድሬዳዋ ከ 250 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ተተክለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ባለፉት አራት ዓመታት የተተከሉ ችግኞች በደን ልማት፣ በምግብ ዋስትና፣ በአፈር ለምነትና መሰል ጉዳዮች ላይ ያመጡትን አዎንታዊ ለውጥ አጥንቶ ይፋ የሚያደርግ ድርጅት መለየቱን ጠቁመዋል።
ከተማዋ ከብክለት የጸዳች ውብና ለኑሮ ተስማሚ ለማድረግ ሁሉም የሚያበረክተውን አዎንታዊ አስተዋጽኦ አጠናክሮ መቀጠል አለበት - ዶክተር ጀማሉ ጀንበሩ
Jun 2, 2023 67
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ) አዲስ አበባ ከተማ ከብክለት የጸዳች ውብና ለኑሮ ተስማሚ ለማድረግ ሁሉም የሚያበረክተውን አዎንታዊ አስተዋጽዖ አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባ ተገለጸ። የዘንድሮው የአለም አካባቢ ቀን በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ50ኛ ጊዜ በኢትዮጵያ ደግሞ ለ30ኛ ጊዜ እየተከበረ ነው። የአካባቢን ጥበቃ ቀንን አስመልክቶ ከግንቦት 25 እስከ ግንቦት 27 የሚቆይ ኢግዚቢሽን ተከፍቷል። በመክፈቻ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማና ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ጀማሉ ጀንበሩ ከተማዋን ምቹ ለማድረግ እየተሰራ ነው ብለዋል። በተለይም በመዲናዋ ነዋሪዎችና በተቋማት የሚመነጩ ደረቅና ፈሳሽ ቆሻሻዎች የተቀመጡ የጽዳት ሕጎች አክብረው እንዲወገዱ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ከተማዋ ከብክለት የጸዳች ውብና ለኑሮ ተስማሚ ለማድረግ ሁሉም የሚያበረክተውን አዎንታዊ አስተዋጽዖ አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ነው ያሳሰቡት። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ዲዳ ድሪባ በበኩላቸው በመዲናዋ የአካባቢ ችግሮች እንዲፈቱ የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ ነው። ለዚህም አካባቢያዊ ደንቦችን፣ ደረጃዎችን መመሪያዎችን በማውጣት በማስተዋወቅ እንዲሁም የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች በስፋት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ጎን ለጎንም ሕግና ደንብ በሚተላለፉ አካላት ላይ እርምጃ እየተሰራ እየተወሰደ መሆኑን ገልጸዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማና ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር ጀማሉ ጀንበሩ ገለጹ።
በአዲስ አበባ በተለያዩ ተቋማት የሚተከሉ 800 ሺህ የሚደርሱ ችግኞች ተዘጋጅተዋል - የጉለሌ እጽዋት ማዕከል
Jun 2, 2023 70
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ)፦ ለዘንድሮው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በአዲስ አበባ በተለያዩ ተቋማት የሚተከሉ 800 ሺህ የሚደርሱ ችግኞችን ማዘጋጀቱን የጉለሌ እጽዋት ማዕከል ገለጸ። የጉለሌ ዕጽዋት ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ጉተማ ሞረዳ ለኢዜአ እንደገለጹት በዘንድሮው ዓመት በአዲስ አበባ በተለያዩ ተቋማት የሚተከሉ 800 ሺህ ችግኞች ተዘጋጅተዋል። በዚህም ችግኝ ለሚያፈሉና ለሚያቀርቡ ዜጎች የሥራ እድል በመፍጠር ወጣቶቹ ገቢያቸውን ማሳድጉን ነው የገለጹት። ማዕከሉ ለዘንድሮው ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አገር በቀል የሆኑ ለአፈርና የውሃ ጥበቃ፣ ለፍራፍሬና ለምግብነት የሚውሉ ጨምሮ አካባቢን ለማስዋብ የሚውሉ ችግኞችን አፍልቶ ማዘጋጀቱን ጠቁመዋል። ማዕከሉ ችግኞችን ከማፍላት ጎን ለጎን ባሉት 705 ሄክታር መሬት ላይ በ2014 ዓ.ም ከተከላቸው ችግኞች ውስጥ 90 በመቶው መጽደቁን ገልጸዋል። በአገር አቀፍ ደረጃ ባለፉት አራት ዓመታት በተካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር 25 ቢሊየን ችግኞች መተከላቸው ይታወሳል። በዘንድሮም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር 6 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኞች ለመትከል ዝግጅት መደረጉን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ መግለጻቸውም እንዲሁ።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የሚኖረው የእርጥበት ሁኔታ ለበልግና ለመኸር ሰብሎች አመቺ ሁኔታ ይፈጥራል - የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት
Jun 2, 2023 60
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ) በሚቀጥሉት አስር ቀናት የሚኖረው የእርጥበት ሁኔታ ለበልግና ለመኸር ሰብሎች እንዲሁም ቋሚ ተክሎች አመቺ ሁኔታ እንደሚፈጥር የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ በቀጣዩቹ አስር ቀናት በተለይም በምዕራብ አጋማሽ የአገሪቱ ክፍሎች ላይ የተስፋፋ የዝናብ መጠንና ሥርጭት ይኖረዋል ብሏል። ይህም በአካባቢዎቹ ላይ እየተከናወነ ለሚገኘውና ለሚጠበቀው የግብርና እንቅስቃሴ በአብዛኛው መልካም ጎን የሚኖረው ሲሆን የሚኖረው የዕርጥበት ሁኔታም የአፈር ውስጥ እርጥበትን ከማሻሻል አንጻር በጎ ሚና የሚጫወት መሆኑም ተመላክቷል። በእነዚህ ቀናት የሚኖረው የእርጥበት ሁኔታ በተለይም ለበልግና ለመኸር ሰብሎች እንዲሁም ቋሚ ተክሎችና የጓሮ አትክልቶች አመቺ ሁኔታ እንደሚፈጥር ነው የተገለጸው። እየተስፋፋ የሚሄደው ዝናብ ሰጪ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታ ቀደም ብለው የመኸር እርሻ እንቅስቃሴን ለጀመሩ አካባቢዎችም ጠቀሜታው ከፍተኛ መሆኑንም እንዲሁ። የሚኖረው እርጥበትም ለአርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮች ለግጦሽና የመጠጥ ውሃ አቅርቦትም የጎላ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተጠቅሷል። እንዲያም ሆኖ በተወሰኑ አካባቢዎች ላይ ከሚጠበቀው ከባድ ዝናብ ጋር ተያይዞ የጎርፍ አደጋ ሊያጋጥም ስለሚችል ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አሳስቧል።
በሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ከ76 በመቶ በላይ የሚሆነውን ቦታ ከልቅ ግጦሽ ነጻ ማድረግ ተችሏል - የፓርኩ ጽህፈት ቤት
Jun 2, 2023 67
ጎንደር ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ):- በሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ከ76 በመቶ በላይ የሚሆነውን የፓርኩን ቦታ ከልቅ ግጦሽና ከእንስሳት ንክኪ ነጻ ማድረግ መቻሉን የፓርኩ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በአውሮፓውያኑ የዘመን ቀመር በ1978 በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) በዓለም የተፈጥሮ ቅርስነት የተመዘገበው ፓርኩ 412 ስኩዌር ኪሎ ሜትር ስፋት አለው። ማራኪና ድንቅ የተፈጥሮ አቀማመጥ ያለው ብሔራዊ ፓርኩ በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኙትን ዋልያ፣ ቀይ ቀበሮና ጭላዳ ዝንጀሮን ጨምሮ የብርቅዬ እጽዋት፣ የዱር እንስሳትና አዕዋፋት መገኛ ስፍራም ነው። የውጭና የአገር ውስጥ ጎብኚዎችን በመሳብ የቱሪዝም ገቢ እያስገኘ ነው። ይሁን እንጂ በፓርኩ ዙሪያ የሚኖሩ ሰዎች ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ በመጨመሩ ለእርሻ፣ ለልቅ ግጦሽና ለቤት መስሪያ በሚል ወደ ፓርኩ በመግባታቸው ብርቅዬ እንስሳት ከፓርኩ ለመራቅ መገደዳቸውን የፓርኩ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አዛናው ታረቀኝ ለኢዜአ ገልጸዋል። በተጨማሪም የፓርኩ አዋሳኝ ከሆኑት አምስት ወረዳዎች ከዚህ ቀደም በሺዎች የሚቆጠሩ የተለያዩ የቤት እንስሳት የግጦሽ ሳር ፍለጋ ወደ ፓርኩ በመግባት ጉዳት ያደርሱ እንደነበር አስታውሰዋል። ፓርኩ የተጋረጡበትን ችግሮች ለመፍታት ባለፉት 10 ዓመታት የልቅ ግጦሽ ቅነሳ ስትራቴጂ ተግባራዊ ማድረጉንና በዚህም ከ76 በመቶ በላይ የሚሆነውን የፓርኩን ክልል ከልቅ ግጦሽና የቤት እንስሳት ንክኪ ነጻ መደረጉን አመልክተዋል። በስትራቴጂው ግብረ ኃይል ከማቋቋም ባለፈ ሕብረተሰቡ እንስሳቱን በቤት ውስጥ አስሮ ቢቀልብ የስጋና የወተት ምርታማነትን በማሳደግ የተሻለ ተጠቃሚ እንደሚሆን ግንዛቤ በመፈጠሩ ፓርኩን ከንክኪ ነጻ ለማድረግ መቻሉን ነው አቶ አዛናው ያስረዱት። አብዛኛው የፓርኩ ክልል ነጻ መደረጉ በውስጡ የሚገኙ ዋልያ፣ ጭላዳ ዝንጀሮዎችና ድኩላዎች ዓመቱን ሙሉ የእጽዋትና የሳር መኖዎችን እንዲያገኙና እንዲባዙ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ገልጸዋል። ከቤት እንስሳቱ ጋር ወደ ፓርኩ ክልል በሚገቡ ውሾች አማካኝነት በቀይ ቀበሮዎች ላይ ይደርስ የነበረውን የእብድ ውሻ በሽታ ስርጭትን በመቆጣጠር የመጥፋት ስጋታቸውን ለመቀነስ እንደተቻለ ተናግረዋል። "በተጨማሪም የዱር እንስሳቱ መኖና ውሃ ፍለጋ ብዙ ኪሎ ሜትሮችን ሲጓዙ ይደርስባቸው የነበረው እንግልት ቀርቷል" ነው ያሉት የፓርኩ ጽህፈት ቤት ኃላፊ። በአሁኑ ወቅት የዱር እንስሳቱ ከቦታ ቦታ በነጻነት ለመንቀሳቀስ የሚያስችላቸው ምቹ ሁኔታ መፈጠሩንና የመራቢያና የመኖሪያ ቦታዎቻቸውንም ከተለያዩ አደጋዎች መጠበቅ መቻሉን ጠቁመዋል። በቀጣይ ፓርኩን ሙሉ በሙሉ ከንክኪ ነጻ ለማድረግም አምባራስ እና አበርጊና በሚባሉ አካባቢዎች ያሉ ነዋሪዎችን ወደ ሌላ አካባቢ ማስፈር እንደሚያስፈልግ የገለጹት አቶ አዛናው ለዚህም መንግስትና የሚመለከታቸው አካላት የበኩላቸውን እገዛ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል። የደባርቅ ከተማ የኢኮ ቱሪዝም ዩኒየን ሊቀመንበር አቶ ሞገስ አየነው በበኩላቸው የቱሪስቶችን እቃዎች የሚያጓጉዙ የዩኒየኑ አባላት ፈረሶችና በቅሎዎች በፓርኩ ውስጥ እንዳይሰማሩ ስምምነት ላይ ተደርሶ መተግበሩን ገልጸዋል። በፓርኩ ለጎብኚዎች አገልግሎት በመስጠት ገቢ እያገኙ ያሉት ከ8 ሺህ በላይ የዩኒየኑ አባላት የፓርኩን ብዝሃ ሕይወት በመጠበቅ እና በመንከባከብ የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን አመልክተዋል። በደባርቅ ወረዳ የሚሊገብሳ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ሙሉቀን ግስሙ የቀበሌው ነዋሪ ለዱር እንስሳቱ ሕልውና ቅድሚያ በመስጠት የግጦሽ ሳር ፍለጋ የቤት እንስሳቶቻችንን ወደ ፓርኩ ክልል ከማሰማራት መቆጠቡን ገልጸዋል።
በመዲናዋ ከሁለት መቶ በላይ ሆቴሎችና የምሽት መዝናኛ ቤቶች ከተፈቀደላቸው በላይ ድምጽ በመጠቀማቸው እርምጃ ተወስዶባቸዋል - የከተማዋ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን
Jun 2, 2023 63
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015 (ኢዜአ) በአዲስ አበባ ከሁለት መቶ በላይ ሆቴሎችና የምሽት መዝናኛ ቤቶች ከተፈቀደላቸው በላይ ድምጽ በመጠቀማቸው እርምጃ መውስዱን የከተማዋ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ገለጸ። የባለሥልጣኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ ድዳ ድሪባ ለኢዜአ እንደገለጹት ባለፉት ሁለት ወራት ከ400 በላይ ሆቴሎችና የምሽት መዝናኛ ቤቶች ላይ የቁጥጥር ሥራ ተሰርቷል። ለዚህም የድምጽ መለኪያ መሳሪያ ሥራ ላይ በማዋልና በቂ ባለሙያዎችን በመመደብ የድምጽ ብክለትን ለመከላከል የሚያስችል ጥብቅ ቁጥጥር መደረጉን ነው የገለጹት። በዚህም በተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ በርካታ ሆቴሎችና የምሽት መዝናኛ ቤቶች የነዋሪውን ጸጥታና ምቾት የሚነሱ መሆናቸውን እንደተደረሰባቸው ጠቁመዋል። ይህንንም ተከትሎ ባለሥልጣኑ በ208 ሆቴሎችና የምሽት መዝናኛ ቤቶች ከተፈቀደላቸው ድምጽ በላይ በመጠቀማቸው የተለያዩ እርምጃ እንደወሰደባቸው ተናግረዋል። እርምጃዎቹ ከማስጠንቀቂያ ጀምሮ እስከ ማሸገ የሚደርስ መሆኑን ጠቁመው ባለሥልጣኑ በእነዚህ የመዝናኛ ቤቶች የሚያደርገውን ቁጥጥር አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። ሆቴሎችና በምሽት መዝናኛ ቤቶች ሕግና ደንብን አክብረው እንዲንቀሳቀሱ የጠየቁት ሥራ አስኪያጁ ከተማዋ ለነዋሪዎች ምቹ እንድትሆን የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል።
ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ከ109 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ተዘጋጅተዋል - የጉራጌ ዞን ግብርና መምሪያ
Jun 1, 2023 70
አዲስ አበባ ግንቦት 24/2015(ኢዜአ)፦ በጉራጌ ዞን ለአምስተኛው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር ከ109 ሚሊየን በላይ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መዘጋጀታቸውን የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለጸ። የመምሪያው ኃላፊ አቶ አበራ ወንድሙ ለኢዜአ እንዳሉት ለግብርና ምርታማነት በተሰጠው ትኩረት በበጋ መስኖ ስንዴና በመደበኛ የመኸር ሰብል ልማት ውጤታማ የምርት አሰባሰብ ስራ እየተከናወነ ይገኛል። በመደበኛ መስኖ ልማት ስራም ከ52 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ በማከናወን 13 ነጥብ 5 ሚሊዮን ኩንታል ሰብል ለመሰብሰብ ታቅዶ ከ14 ነጥብ 1 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል። በመደበኛ የመስኖ ልማት የተቀመጠውን ግብ ከዕቅድ በላይ በማሳካት እንደ ቲማቲም፣ ጥቅል ጎመን፣ ካሮት፣ ሽንኩርት ሌሎች የአትክልትና ፍራፍሬ ዓይነቶችን ማልማት መቻሉንና የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት በዞኑ የምርታማነት ልማት ስራ እየተሻሻለ መምጣቱን አመልክተዋል። በተያዘው በጀት ዓመት ባለፉት ወራትም ከ2 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት የበጋ መስኖ ስንዴን በማልማት እስካሁን ከ80 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት መሰብሰብ እንደተቻለ ጠቁመዋል። ለአምስተኛው የአረንጓዴ አሻራ ልማት መርሃ-ግብር ቅድመ ዝግጅትም እንደዞን ከ109 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ-ብዙ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኝ መዘጋጀታቸውንና ከዚህም ውስጥ ከ1 ነጥብ 2 ሚሊየን በላይ የሚሆኑ የፍራፍሬ ችግኞች እንደሚገኝበት ነው አቶ አበራ ያስረዱት። የፍራፍሬ እጽዋቶችን ማልማት የአርሶ አደሩን የምግብ ፍጆታ በማረጋገጥ የገበያ አማራጭ መፍጠር እንደሚያስችል አመልክተዋል። ለመርሐ-ግብሩ ከ18 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኝ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። በአገር አቀፍ ደረጃ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በተያዘው አምስተኛ ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር 6 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኞች መዘጋጀታቸውን በመጠቆም፤ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞችን በብዛት እንደሚተከሉ ማሳወቃቸው የሚታወስ ነው።
በሲዳማ ክልል በአምስተኛው ዙር አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ94 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ተተክለዋል
Jun 1, 2023 66
ሀዋሳ፣ ግንቦት 24 ቀን 2015 (ኢዜአ) በሲዳማ ክልል በአምስተኛው ዙር አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ከ94 ሚሊዮን በላይ ችግኞች መተከላቸውን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ገለጸ። የችግኞቹን መጠነ ጽድቀት ከፍ ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎችም ከወዲሁ እየተሰሩ እንደሆነ ተጠቁሟል። የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ፍቅረኢየሱስ አሸናፊ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በክልሉ በዘንድሮ መርሃ ግብር 316 ሚሊየን ችግኞችን ለመትከል ታቅዷል። ከሚያዚያ ወር ወዲህ አርሶ አደሮችን ጨምሮ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በተካሄደ ንቅናቄ የእቅዱን 30 በመቶ መፈጸም መቻሉን ገልጸዋል። አብዛኛዎቹ የተተከሉት ችግኞች የአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖን ለመቋቋም አስተዋጽኦ ያላቸው እንደሆነ ጠቅሰው፤ እንደ ዋንዛ፣ ግራር፣ ጽድ፣ ቢርቢራ የመሳሰሉ ሀገር በቀል እና ለአርሶ አደሩ በቋሚነት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የቡናና የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ተናግረዋል። በክልሉ ለችግኝ ተከላ የሚሆኑ ከ200 በላይ ተራራዎች፣ የተራቆቱ አካባቢዎችና ሌሎችም መትከያ ስፍራዎች ተለይተው ከክልል ጀምሮ ባሉ ሁሉም መዋቅሮች ንቅናቄ በመፍጠር ዕቅዱን ለማሳካት እየተሰራ እንደሆነ አመልክተዋል። ለተተከሉት ችግኞች እንክብካቤ በማድረግ እንዲጸድቁ እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። እንደ ምክትል ቢሮ ኃላፊው ገለፃ፤ በክልሉ ባለፉት አራት ዓመታት አረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ከ850 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መትከል ተችሏል። ይህም ለአፈርና ውሃ እቀባ እንዲሁም የመሬትን ለምነትና እርጥበትን በማሻሻል ለምርትና ምርታማነት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አስረድተዋል። ከተተከሉት ፍራፍሬዎች መካከል የተሻሻሉ የአቮካዶ ዝርያዎች ምርት በመስጠት ለይርጋለም የተቀናጀ ግብርና ፓርክ ግብዓት ሆኖ እየቀረበ እንደሆነም ተናግረዋል። የዳራ ሆጢልቾ ወረዳ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ መንግስቱ ማቲዎስ በበኩላቸው ለዘንድሮ አረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ስኬታማነት በትኩረት እየተሰራ እንደሆነ ገልጸዋል። ወረዳው ዘንድሮ 5 ነጥብ 4 ሚሊዮን ችግኝ ለመትከል ማቀዱን ጠቅሰው፤ እስካሁን 2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ችግኝ መትከል መቻሉን አመልክተዋል። ቀሪውን ችግኝ ለመትከል በህብረተሰብ ተሳትፎ የችግኝ ጉድጓድ ቁፋሮ በዘመቻ እየተካሄደ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በችግኝ ተከላ ተራቁቶ የነበረ ከ736 ሄክታር በላይ መሬት መልሶ በማገገም ወደ ልማት መግባቱን ጠቅሰው፤ በወረዳው የችግኝ መጠነ ጽድቀት 92 በመቶ መድረሱን ተናግረዋል። እየተከናወነ ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለመሬት እርጥበትና ለምነት ጉልህ ሚና እየተጫወተ ነው ያሉት ደግሞ የብላቴ ዙሪያ ወረዳ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ላሚሶ ዴራሞ ናቸው። ልማትን በተቀናጀ መንገድ መምራት የሚያስችል ንቅናቄ ተፈጥሮ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ዘንድሮ 2 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ ችግኝ በወረዳው ይተከላል ብለዋል።
በጅማና ምስራቅ ወለጋ ዞኖች ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ቅድመ ዝግጀት ስራ እየተጠናቀቀ መሆኑ ተገለጸ
Jun 1, 2023 68
ጅማ/ነቀምት ግንቦት 24/2015:-በጅማና ምስራቅ ወለጋ ዞኖች ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ቅድመ ዝግጀት እየተጠናቀቀ መሆኑን የየዞኖቹ ግብርና ጽህፈት ቤቶች ገለጹ። በጅማ ዞን ብቻ ለ5ኛው ዙር የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሀ ግብር ከ350 ሚሊዮን በላይ ችግኞች የሚተከሉ መሆኑ ተገለጿል። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ መሀመድ ጣሃ አባፊጣ እንደተናገሩት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ በዘመቻ እንዲሁም በተቋማት አማካይነት የሚከወን መሆኑንና የመትከያ ቦታዎች እየተዘጋጁ ስለመሆኑ ገልጸዋል። በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከዚህ ቀደም በዞኑ ያልተለመዱ እንደ ቀርቃሃ እና ቴምር ያሉ ችግኞችም የሚተከሉ ይሆናል ብለዋል። ከዚህ ቀደም የተተከሉ ችግኞችን ከመንከባከብ አንጻር የጽድቀት መጠኑ 80 በመቶ ሲሆን ይህም የሚበረታታ መሆኑን ነው ሀላፊው የተናገሩት። በዞኑ የነዲ ጊቤ ወረዳ ነዋሪ ወይዘሮ ነዚፋ አወል፣ በዚህኛው ዙር 100 ችግኝ ለመትከል ቦታ ያዘጋጁ መሆኑን እና በዘመቻ የሚተከለውንም ለመሳተፍ ተዘጋጅተዋል። ሌላው የዴዶ ወረዳ አርሶ አደር ወጣት ናስር አባ ጀበል በበኩሉ በየአመቱ የተለያዩ ችግኞችን በማሳው ዳርቻ እንደሚተክል ገልጾ ዘንድሮም 50 የተመረጡ የዛፍ ችግኞችን ለመትከል መዘጋጀቱን ተናግሯል። ''ከዚህ በፊት የተከልኳቸውን ችግኞች በመንከባከብ ጥሩ ደረጃ ላይ ደርሰዋል'' ያለው ወጣቱ ''አሁንም እንደ ዋንዛ እና ግራር የመሳሰሉ ዞፎችን እተክላለሁ'' ብሏል። በተመሳሳይ በምሰራቅ ወለጋ ዞን በመጪው ክረምት 400 ሚሊዮን ችግኞች መዘጋጀታቸውን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገልጿል፡፡ በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት ስራ ሂደት ሃላፊ አቶ ደሳለኝ በለታ በዞኑ በተለያዩ ወረዳዎች የችግኝ እና ጉድጓድ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። እሰካሁን በተሰራ ስራ በ2 ሺህ 148 ችግኝ ጣቢያዎች 378 ሚልዮን ችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። እየተዘጋጁ ከሚገኙት ችግኞች መካከል ለእንስሳት መኖ፣ ቀርከሃ፣ ፍራፍሬ እና የተለያዩ ዛፎች ይገኙበታል ብለዋል፡፡ በዞኑ ለዚሁ አላማ የሚውል 39 ሺህ ሔክታር መሬት ተዘጋጀ ሲሆን 182 ሚልዮን የችግኝ መትከያ ጉድጓድ መዘጋጀቱን ጠቅሰዋል።
ኢትዮጵያ እያካሄደች ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሌሎች የአፍሪካ አገራት አርአያ የሚሆን ነው - ኢሲኤ
Jun 1, 2023 111
አዲስ አበባ ግንቦት 24/2015 (ኢዜአ):- ኢትዮጵያ እያካሄደች ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሌሎች የአፍሪካ አገራት ምሳሌ የሚሆን ነው ሲሉ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን የቴክኖሎጂ፣ የአየር ንብረት ለውጥና የተፈጥሮ ሃብት ዳይሬክተር ዦን ፖል አደም ተናገሩ። ዳይሬክተሩ ዦን ፖል አደም ለኢዜአ እንደገለጹት ኢትዮጵያ የምታካሂደው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የብዝሃ ሕይወት ጥበቃን ለማረጋገጥ ወሳኝ ነው። ያም ብቻ ሳይሆን በመርሃ ግብሩ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥና የኑሮ ሁኔታ ለማሻሻል የሚያስችሉ ተግባራት ማቀፉንም ነው የጠቆሙት። ለአብነትም ለበርካታ ዜጎች የሥራ እድል ለመፍጠር የሚያስችሉ ቡናን ማልማትና ሌሎችም ኢኮኖሚያዊ አንድምታ ያላቸው እንቅስቃሴዎች እንዳሉት ተናግረዋል። ጎን ለጎንም ኢትዮጵያ በተፋሰስ አካባቢ ብዝሃ ሕይወት በመንከባከብ የውሃ ሃብትን ለመንከባከብ እየሰራች ያለው ሥራ የሚደነቅ መሆኑንም አንስተዋል። በመሆኑም ይህ ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያለው የአረንጓዴ አሻራ ለሌሎች የአፍሪካ አገራት በአርአያነት የሚጠቀስ መርኃ ግብር መሆኑን ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። ተቋማቸውም ይህንን የኢትዮጵያ ጥረት ስኬታማ ለማድረግ የሙያ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የአፍሪካ አገራት ኢኮኖሚያዊ ለውጥን እውን ለማድረግ የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ ዋነኛው መሆኑን ገልጸው በዘርፉ ሕዝቡን በበቂ ሁኔታ ተጠቃሚ ሳይሆን መቆየቱን ጠቁመዋል። በመሆኑም የአፍሪካ አገራት ለዘርፉ አስፈላጊውን ትኩረትና በመስጠትና ከዘርፉ የሚያገኙትን ጥቅም ከፍ በማድረግ የሕዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት። የአፍሪካ አገራት በግብርናው ዘርፍ ዘላቂነት ያለው የእሴት ሰንሰለት በመፍጠር በቱሪዝም ዘርፍ ገቢን ማሳደግ እንደሚገባ ዳይሬክተር ዦን ፖል አደም ተናግረዋል።
የኢንዱስትሪ ፓርኮች በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያላቸውን ተሳትፎ ለማጠናከር እየተሰራ ነው - የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን
May 31, 2023 87
አዲስ አበባ ግንቦት 23/2015 (ኢዜአ) የኢንዱስትሪ ፓርኮች በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያላቸውን ተሳትፎ ለማጠናከር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ገለጸ። የኮርፕሬሽኑ የኮሚዩኒኬሽንና ማርኬቲንግ መምሪያ ኃላፊ ዘመን ጁነዲ ኮርፖሬሽኑ የአገሪቱን መዋቅራዊ ሽግግር እውን ለማድረግ ከመስራት ጎን ለጎን ለአካባቢ ጥበቃና ሥነ-ምህዳር መጠበቅ የራሱን አበርክቶ እየተወጣ ነው። ባለፉት አራት ዓመታት በተካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በኢንዱስትሪ ፓርኮቹ ከ2 ሚሊየን በላይ ችግኞች መተከላቸውን ተናግረዋል። ችግኞቹ ተገቢውን ጥበቃና እንክብካቤ ሲደረግላቸው የቆየ መሆኑን አስታውሰው፤ የፅድቀት መጠናቸውም ከ90 በመቶ በላይ መሆኑን አስረድተዋል። ኮርፖሬሽኑ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ከ1 ሚሊየን በላይ የተለያዩ ዝርያ ያላቸውን የዛፍ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም የኢንዱስትሪ ፓርኮች በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያላቸውን ተሳትፎ ለማጠናከርና ለማሳደግ በትኩረት እንደሚሰራ ነው የገለጹት። የቦሌ ለሚ ኢንዱስትሪ ፓርክ የፋይናንስና አስተዳደር አገልግሎት ኃላፊ ሲሳይ አስፋው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተቋማትን በአረንጓዴ ዕጽዋቶች በማስዋብ ጽዱና ምቹ የሥራ ከባቢን ለመፍጠር ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል። መርሃ ግብሩ ከተጀመረ ጊዜ አንስቶ ሰራተኞች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች በመትከልና በመንከባከብ በንቃት እየተሳተፉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በ5ኛው ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም በንቃት ለመሳተፍ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በቦሌ ለሚ ኢንዱስትሪ ፓርክ የፈሳሽ ማጣሪያ አስተባባሪ ሰይፈ ፈረደ በበኩላቸው ከፋብሪካው የሚወጣው የታከመ ውሃና የደረቅ ቆሻሻ ብስባሽ ለሚተከሉት ችግኞች ህይወት መስጠቱን ተናግረዋል። በአገር አቀፍ ደረጃ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ባለፉት አራት ዓመታት 25 ቢሊየን ችግኞች የተተከሉ ሲሆን፤ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ደግሞ ከ7 ቢሊየን በላይ ችግኞች ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ ይታወቃል።
የዓለም የአካባቢ ጥበቃ ቀን በመዲናዋ በተለያዩ መርሐ-ግብሮች ለማክበር ዝግጅት ተደርጓል-የአዲስ አበባ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን
May 30, 2023 77
አዲስ አበባ ግንቦት 22/2015 (ኢዜአ)፦ የዓለም የአካባቢ ጥበቃ ቀን በመዲናዋ በተለያዩ መርሐ-ግብሮች ለማክበር ዝግጅት መደረጉን የአዲስ አበባ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ። የዓለም የአካባቢ ጥበቃ ቀን ''የፕላስቲክ ብክለት መፍትሄ'' በሚል መሪ ሀሳብ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ50ኛ ጊዜ በኢትዮጵያ ደግሞ ለ30ኛ ጊዜ ከግንቦት 25 እስከ ግንቦት 27 ቀን 2015 ይከበራል። የአዲስ አበባ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ድዳ ድሪባ ቀኑን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ፤ ቀኑ በአዲስ አበባ በከተማ ደረጃ በፓናል ውይይት፤ችግኝ ተከላ እንዲሁም በተለያዩ አውደ ርዕዮች እንደሚከበር አስታውቀዋል። የአካባቢ ጥበቃ ቀን በየዓመቱ ግንቦት 28 ቀን የሚከበር ሲሆን ዘንድሮ በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕለቱ በምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር ኮትዲቭዋር እንዲሚከበር ተገልጿል። በዓለም አቀፍ ደረጃ በየዓመቱ ከ400 ሚሊዮን ቶን ፕላስቲክ የሚመረት ሲሆን፤ ከዚህም ውስጥ ግማሽ የሚሆኑት ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም የሚውሉ መሆናቸውን መረጃዎች ያመላክታሉ፡፡ በኢትዮጵያም የፕላስቲክ ምርቶች ለአካባቢ ብክለት መንስኤ እየሆኑ መምጣታቸው ይነገራል። ለአብነትም በየዓመቱ ወደ ከ900 ሺህ ቶን በላይ አዳዲስ የፕላስቲክ ማሸጊያዎችን ወደ አገር ውስጥ የሚገቡ ሲሆን፤ ከዚህም ውስጥ መልሶ ጥቅም ላይ የሚውለው ከአምስት በመቶ እንደማይበልጥ መረጃዎች ያሳያሉ።
የአፍሪካ ሕብረት የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ ስብሰባ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው
May 30, 2023 99
አዲስ አበባ ግንቦት 22/2015 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሕብረት የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ ስብሰባ በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ነው ። በሕብረቱ ኮሚሽን የተዘጋጀው ስብሰባ የአፍሪካ፣ ካሪቢያንና ፓስፊክ የብዝሃ ህይወት አለም አቀፍ ስምምነት፣ የኮፕ-15 የተባበሩት መንግስታት የብዝሀ ሕይወት ስብሰባና 19ኛው በንግድ እንቅስቃሴ ምክንያት እንስሳትና እጽዋት ላይ ጉዳት ላለማድረስ የተደረገ ስምምነት ስብሰባ ውጤቶች ትግበራ ላይ ያተኮረ ነው። የአፍሪካ ሕብረት የዘላቂ አካባቢ ጥበቃና ብሉ ኢኮኖሚ ዳይሬክተር ሀርሰን ኒያምቢ ብዝሃ ሕይወት በአፍሪካ ለቱሪዝም፣ ለመድኃኒት (ፋርማሲዩቲካል) ኢንዱስትሪ እና ንግድ ዘርፍ ያለው ፋይዳ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ከብዝሃ ሕይወት የአካባቢን ማህበረሰብ በሚፈለገው መልኩ ተጠቃሚ አለመሆን፣ ሕገ-ወጥ ንግድ እና የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖ በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮች ናቸው ብለዋል። በመሆኑም በዓለም የብዝሃ ሕይወት ስብሰባ ውጤቶችንና ስምምነቶችን በቅንጅት መስራት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል። በብዝሃ ሕይወት ላይ ትኩረት ያደረጉ መርሐ-ግብሮችን፣ የእንስሳትና እጽዋት ሕገ-ወጥ ንግድን ለመከላከል የተዘጋጀውን ስትራቴጂና ቀጣይነት ያለው የደን አስተዳደር ማዕቀፍን መተግበር እንደሚያስፈልግ ነው ዳይሬክተሩ ያመለከቱት። የአውሮፓ ሕብረት ተወካይ አውሬሊ ጎዴፍሮይ አፍሪካ የብዝሃ ሕይወትና አካባቢ ጥበቃ ድጋፉን እንደሚቀጥል ገልጸዋል። ለአፍሪካ ቀጣይነት ያለው የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ እና አጠቃቀም ዓለም አቀፍ ትብብርና ጥምረትና የገንዘብ ድጋፍ ወሳኝ እንደሆኑም አመልክተዋል። የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የቴክኖሎጂ፣ አየር ንብረት ለውጥና የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ዳይሬክተር ጂን ፓል በበኩላቸው አገራት ቀጣይነት ያለው የብዝሃ ሕይወት እንዲኖር እያከናወኑ ያለውን ተግባር ያነሱ ሲሆን ኢትዮጵያ እያከናወነች ያለው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር ተጠቃሽ መሆኑን አንስተዋል። በባለሙያዎች ደረጃ የተጀመረው ስብስባ እስከ ነገ ይቆያል። በሚኒስትሮች ደረጃ የሚደረገው ስብስባ ከነገ በስቲያ የሚጀመር ሲሆን በባለሙያዎች ደረጃ በቀረቡላቸው አጀንዳዎች ላይ ይመክራሉ ተብሎ ይጠበቃል።
በዞኑ ከ180 ሚሊዮን በላይ ችግኝ መትከል የሚያስችል ጉድጓድ መዘጋጀቱ ተገለጸ
May 30, 2023 104
አዳማ ግንቦት 22/2015 (ኢዜአ) በምስራቅ ሸዋ ዞን በአረንጓዴ አሻራ መርሓ ግብር ከ180 ሚሊዮን በላይ ችግኝ መትከል የሚያስችል ጉድጓድ መዘጋጀቱን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለፀ። በዞኑ አቃቂ ወረዳ ቢልብሎ ቀበሌ በመጪው ክረምት ለሚከናወነው አምስተኛው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የችግኝ መትከያ ጉድጓድ ዝግጅት ትናንት ተካሂዷል። የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ መስፍን ተሾመ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት በዞኑ ከ260 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ ችግኞች መትኪያ ጉድጓድ ለማዘጋጀት ታቅዶ እየተሰራ ነው ብለዋል። በእስከ አሁኑ ሂደት 182 ሚሊዮን ጉድጓድ መዘጋጀቱን የገለፁት ሃላፊው ከእቅዱ 70 በመቶ ተሳክቷል ነው ያሉት። በዞኑ 11 ወረዳዎች በሚገኙ 292 ተፋሰሶች ተለይተው ችግኝ መትከያ ጉድጓድ እየተዘጋጀ መሆኑን ጠቅሰው በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ አገልግሎት የሚሰጡ የቆላ ዛፎች በስፋት ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል። በዚህም ቴምር፣ ቀርከሃ፣ ግሽጣ፣ ዜይቱንና ሌሎች ዛፎች እንዲሁም የእንስሳት መኖ እንደሚገኝበትም ገልጸዋል። በችግኝ ጉድጓድ ዝግጅቱ አርሶ አደሮች፣ አርብቶ አደሮች፣ ሴቶችና ወጣቶች፣ ተማሪዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸዋል። 52 የመንግስት የችግኝ ጣቢያዎችን ጨምሮ በ1ሺህ 900 የግለሰቦችና ማህበራት የተለያዩ አገልግሎት የሚሰጡ ከ260 ሚሊዮን በላይ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። የምስራቅ ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አባቡ ዋቆ በበኩላቸው የችግኝ ዝግጅቱ ከሰውና እንስሳት ንኪኪ ነፃ የሆኑና ባለፈው በጋ የእርከን ማሰርና የተፋሰስ ልማት የሰራንባቸው ተራራዎችና የተራቆቱ ቦታዎች ላይ ነው ብለዋል። ዘንድሮ የሚተከሉ ችግኞች እንደ ከዚህን በፊቱ የደን ልማት ብቻ ላይ ትኩረት ያደረጉ ሳይሆን ለምግብነትና ለአፈር ለምነት ጨምር ትልቅ ፋይዳ ያላቸውን ችግኞች በስፋት ለመትከል ዝግጅት እየተጠናቀቀ ነው ብለዋል። ''የጉድጓድ ዝግጅት እያከናወንበት ያለው የቢልብሎ ተራራ ከአምስት ዓመት በፊት የተራቆተና ምንም አይነት የዛፍና የሳር ዝርያ የሌለበት ነው'' ያሉት አቶ አባቡ ''በአረንጓዴ አሻራ ላይ በሰራ ነው ስራ ዛሬ የምታዩትን ውጤት አግኝተናል'' ነው ያሉት ። በዚህም የተራቆቱ መሬቶች መልሶ አገግመዋል፣ ወንዞችና ዥረቶች መመለስ ከመቻላቸው ባለፈ ከቢልብሎ ተራራ ክረምቱን እየወረደ አርሶ አደሩ የሚቸገርበትን ጎርፍ ማስቀረት እንደተቻለም ገልጸዋል። በአቃቂ ወረዳ የቢልብሎ ቀበሌ ነዋሪ ወጣት መኮንን ቱፋ በበኩሉ ቢልብሎ ተራራ ምንም አይነት ዛፍና ሳር ያልነበረበት ያገጠጠና የተራቆተ ቦታ ነበር ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በእርከን ማሰር፣ በተፋሰስ ልማትና በአረንጓዴ አሻራ በሰራነው ስራ ተራራው ተመልሶ በደን እየተሸፈነ ከመሆኑም ባለፈ የደረቁ ወንዞችና ዥረቶች ተመልሰው አሁን እየተጠቀሙበት መሆኑን አውስተዋል።
በጋምቤላ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብር ከ11 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ ነው - ቢሮው
May 27, 2023 138
ጋምቤላ ግንቦት 19 /2015 (ኢዜአ)፡- ዘንድሮው በሚካሄደው አምስተኛው ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በጋምቤላ ክልል ከ11 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ አስታወቀ። እየተዘጋጁ ከሚገኙት ውስጥ ከ50 ከመቶ በላይ የሚሆኑት ለሌማት ቱሩፋት ስኬታማነት የሚያግዙ የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ቢሮው ገልጿል። የቢሮው ኃላፊ አቶ አጃክ ኡቻላ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተራቆቱ አካባቢዎችን ወደ ቀድሞው ይዞታ በመመለስ ምርታማነትን ለማሳደግ በትኩረት እየተሰራ ነው። ዘንድሮ በሚካሄደው አምስተኛው ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በክልሉ ከ11 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ገልጸው፤ እስካሁን ባለው ሂደት ከ10 ሚሊዮን በላይ ለተከላ መሰናዳቱን አስታውቀዋል። በክልሉ ዘንድሮ ከሚተከሉት ችግኞች መካከል ከ50 ከመቶ በላይ የሚሆኑት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መሆናቸውን አስረድተዋል። ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ካላቸው ችግኞች መካከል ማንጎ፣ አቡካዶ፣ ብርቱካንና ፓፓያ እንደሚገኙበት ጠቅሰው፤ እነዚህም የሌማት ቱሩፋት መርሃ ግብርን ስኬታማ ለማድረግ የሚያግዙ የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ገልጸዋል። ችግኞቹ በ2 ሺህ 496 ሄክታር በተራቆቱ አካባቢዎችና በቤት ጓሮ አካባቢዎች የሚተከሉ ይሆናል ብለዋል። በክልሉ በአራተኛ ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተተከሉት ከ10 ሚሊዮን በላይ ችግኞች መካከል በተደረገላቸው እንክብካቤ 86 በመቶ መጽደቃቸንውም አቶ አጃክ ገልጸዋል። በጋምቤላ ክልል ባለፉት አራት ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተተከሉ ከ24 ነጥብ 5 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ከ17 ሺህ 980 ሄክታር በላይ የተራቆተ መሬት በደን መሸፈን እንደተቻለ ከክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ የተገኘው መረጃ ያሳያል።
ሀገር በቀል ዕፅዋትንና እንስሳትን ጨምሮ የብዝኃ ሕይወት መመናመንን ለማስቀረት ማህበረሰቡን ያሳተፈ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃን ማጠናከር ይገባል -ተመራማሪዎች
May 27, 2023 173
አዲስ አበባ ግንቦት 19/2015(ኢዜአ):- ሀገር በቀል ዕፅዋትንና ብርቅዬ እንስሳትን ጨምሮ የብዝኃ ሕይወት መመናመንን ለማስቀረት ማህበረሰቡን ያሳተፈ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃን ማጠናከር እንደሚገባ የዘርፉ ተመራማሪዎች ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ብዝኃ ህይዎት ኢንስቲትዩት በበኩሉ የብዝኃ ሕይወት ሀብቶችን ጠብቆ ለማቆየት የመገኛ አካባቢያቸውን የማስጠበቅና ዝርያዎችን በማዕከላት የማንበር ተግባራትን እያከናወንኩ ነው ብሏል። ምሁራኑ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የሰው ልጅ ሕልውና ዋስትና የሆነው ብዝኃ ሕይወት የሕልውና አደጋ ተደቅኖበታል ብለዋል። ለብዝኃ ሕይወት አደጋ ለይ መውደቅና መመናመን የኢንዱስትሪ መስፋፋትን እና የህዝብ ቁጥር መጨመርን እንደ ምክንያትነት አንስተዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የብዝኃ ሕይወት ተመራማሪው ፕሮፌሰር ሰብስቤ ደምሰው፤ የአየር ንብረት መዛባት ለብዝኃ ህይወት መመናመን አንዱ መንስኤ መሆኑን ጠቅሰዋል። የብዝኃ ሕይወትን ለመታደግ እንደ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያሉ ማህበረሰቡን የሚያሳትፉና ተጠቃሚነቱን የሚያረጋግጡ ተግባራትን ማጠናከርና ግንዛቤን ማስፋት ይገባል ነው ያሉት። የመሬት ይዞታ አጠቃቀምን ማስተካከልም ሌላኛው ለብዝኃ ህይወት መጠበቅ መፍትሔ መሆኑን አንስተዋል። በሰላሌ ዩኒቨርሲቲ የብዝኃ ሕይወት ተመራማሪ የሆኑት ፕሮፌሰር አየሁ ፈቃዱ እንደሚሉት፤ የህዝብ ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ መምጣቱ ለብዝኃ ህይወት መመናመን መንስኤ መሆኑን ተናግረዋል። አንዳንድ የዕፅዋት ዝርያዎች ለመጥፋት መቃረባቸውን ጠቅሰው፤ይህን ስጋት ለመቀልበስ የብዝኃ ሕይወት ጥበቃ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል። በዚህም አርሶ አደሩ እየተሳተፈባቸው ያሉ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ ጠቁመዋል። የብዝኃ ሕይወት ማገገም ስራ ሲሰራ ከቦታ መረጣ ጀምሮ ማህበረሰቡን ማወያየትና በባለቤትነት እንዲሳተፍ መንግስት በትኩረት እንዲሰራም አመላክተዋል። በከተማ መስፋፋት፣ በእርሻ መሬት መስፋፋት ምክንያት የመጥፋት አደጋ እየተጋረጠባቸው ያሉት የእንስሳት እና የዕፅዋት ዝርያዎችን ህልውና ለመታደግ፤ በጥናት ላይ የተመሰረተ ልዩ እቅድ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። ለዚህም በምርምር ተቋማት የተካሄዱ ጥናቶችን ወደ ተግባር ማስገባት እንደሚገባ አስረድተዋል። በጅንካ ግብርና ምርምር ማዕከል ተመራማሪ ምትኩ አየለ በበኩላቸው፤ በተለያዩ ምክንያቶች በደኖች ላይ የሚደርሰው ጉዳት አጠቃላይ ብዝኃ ሕይወት እንዲመናመን እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ይህንን ችግር ለመከላከል በዋናነት ዛፎችን በመትከል እና የአፈር ለምነትን በማሻሻል የደን ሽፋንን ማሳደግ እንደሚገባ ምክረ ሀሳባቸውን ሰጥተዋል። የኢትዮጵያ ብዝኃ ህይዎት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ፈለቀ ወልደየስ፤ የኢትዮጵያ ብዝኃ ሕይወት ሀብት የሕልውና አደጋ እያጋጠመው መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢንስቲትዩቱ ሀገር በቀል ዕፅዋትን እና በኢትዮጵያ ብቻ የሚገኙ እንስሳትን ጨምሮ የብዝኃ ሕይወት ሀብትን ጠብቆ ለማቆየት የመገኛ አካባቢያቸውን የማስጠበቅና ዝርያዎችን በማዕከላት የማንበር ተግባራትን እያከናወነ ነው ብለዋል።
በሐረሪ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከል 2 ሚሊዮን ችግኝ መዘጋጀቱን የግብርና ልማት ቢሮ አስታወቀ
May 25, 2023 153
ሐረር ግንቦት 17 /2015(ኢዜአ) ፡- በሐረሪ ክልል በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብር የሚተከል 2 ሚሊዮን ችግኝ መዘጋጀቱን የክልሉ ግብርና ልማት ቢሮ አስታወቀ። ከዚህ ውስጥ 70 በመቶ የፍራፍሬና 30 በመቶ ደግሞ የደን ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን በግብርና ልማት ቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ዳይሬክቶሬት ተወካይ አቶ ሙህየዲን መሃመድ ለኢዜአ ገልጸዋል። እስካሁን በተደረገው እንቅስቃሴ ከተዘጋጀው 2 ሚሊዮን ችግኝ 1 ነጥብ 4 ሚሊዮን የፍራፍሬ መሆኑን አመልክተው፤ የችግኝ መትከያ ጉድጓድ ቁፋሮ ዝግጅትም ከወዲሁ መጀመሩን አስታውቀዋል፡፡ ከፍራፍሬ ችግኙ መካከል ፓፓዬ፣ አቮካዶና ዘይቱና እንደሚገኝበት ጠቅሰው፤ 120 ሺህ የሐረር ቡና ችግኝ ለመትከል ታቅዶ እስካሁን ባለው ሂደት 85 ሺህ የቡና ችግኝ መሰናዳቱን አስረድተዋል፡፡ በተለይ ዘንድሮ የሚተከለው የፓፓዬ ችግኝ በዘጠኝ ወራት ውስጥ ፍሬ የሚሰጥ ዝርያ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፈው ዓመት የተተከለው የፓፓዬ ችግኝ ለፍሬ ደርሶ በአሁኑ ወቅት ምርቱ ለገበያ እየቀረበ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብር በሚከናወነው የችግኝ ተከላ ላይ ህብረተሰቡ የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርግ ከወዲሁ የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራ መከናወኑን ያመለከቱት አቶ ሙህየዲን፤ በቀጣዩ ሳምንት የፓፓዬ ችግኝ ለማሰራጨት ዝግጅት መደረጉን አስታውቀዋል፡፡ ዝናቡ ከወቅቱ ቀደም ብሎ መጣል መጀመሩ ዘንድሮ የሚተከለው ችግኝ የመፅደቅ መጠንን ከፍ ያደርገዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡ ግንቦት 29 ቀን 2015ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የመክፈቻ ሥነ-ሥርዓት ለማካሄድ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አቶ ሙህየዲን አብራርተዋል፡፡ በክልሉ የኤረር ቂሌ ችግኝ ጣቢያ አስተባባሪ አቶ ዘሪሁን አያሌው በበኩላቸው፤ በጣቢያው የደን፣ የተዳቀለ የአቮካዶና የማንጎ ችግኝ እየተዘጋጀ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ እስካሁን በጣቢያው 1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ችግኝ መዘጋጀቱን አመልክተዋል።
የአየር ንብረት ለውጥ በግብርና ልማት ላይ የሚያደርሰውን ተጽእኖ ለመከላከል የምርምር ማዕከላትን ጥምረት በማጠናከር በትብብር መስራት ይገባል- ዓለም አቀፉ እንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩት
May 25, 2023 154
አዲስ አበባ ግንቦት 17/2015(ኢዜአ)፡- የአየር ንብረት ለውጥ በግብርና ልማት ላይ የሚያደርሰውን ተጽእኖ ለመከላከል ዓለም አቀፍ የምርምር ማዕከላትን ጥምረት በማጠናከር በትብብር መስራት እንደሚገባ ዓለም አቀፉ የእንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩት ገለጸ፡፡ በኢትዮጵያ በአነስተኛ እርሻ ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮችን አቅም ለማጎልበት የሚደረገውን የግብርና መዋቅራዊ ለውጥ በተመለከተ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት የተሳተፉበት አውድ ጥናት ተካሂዷል፡፡ የዓለም አቀፉ እንስሳት ምርምር ማዕከል በኢትዮጵያ ተወካይ ዳይሬክተር ዶክተር ናሙኮሎ ኮቪች፤ ኢትዮጵያን ጨምሮ በቀጣናው ሀገራት በአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ ለከፋ ድርቅና የጎርፍ አደጋ እየተጋለጡ ነው ብለዋል። በዚህም በዝቅተኛ እርሻ ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች በምርምር የታገዘ ድጋፍና ክትትል ካልተደረገላቸው ችግሩን መቋቋም ይሳናቸዋል ብለዋል፡፡ በመሆኑም መንግስታት፣ የዘርፉ ተዋንያንና ተመራማሪዎች እንደ ዓለም አቀፉ የግብርና ምርምር ማዕከላት ጥምረት ያሉ ተቋማትን አቅም ማጎልበት እንደሚጠበቅባቸው ገልጸዋል፡፡ በአነስተኛ እርሻ የሚተዳደሩ አርሶ አደሮች ላይ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያደርሰውን ተጽእኖ ለመከላከል ዓለም አቀፍ የግብርና ምርምር ማዕከላትን ጥምረት በማጠናከር በትብብር መስራት ያስፈልጋል ነው ያሉት። የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ማንደፍሮ ንጉሴ፤ በኢትዮጵያ 11 የሚደርሱና በተለያዩ ዘርፍ የተሰማሩ የዓለም አቀፍ የግብርና ምርምር ማዕከላት ጥምረት ተቋማት እንዳሉ ገልጸዋል፡፡ እነዚህ ተቋማት በግብርና፣ በአየር ንብረት ለውጥ፣ በምግብ ዋስትና መሰል ጉዳዮች ላይ የተሟላ ጥናትና ምርምር በማካሄድ መረጃና ምክረ ሀሳብ የሚያቀርቡ ናቸው ብለዋል፡፡ የምርምር ተቋማቱ በኢትዮጵያ እንዲሁም በቀጣና እና ዓለም አቀፍ ደረጃ የአየር ንብረት ለውጥን በተመለከተ ጥናትና ምርምር በማድረግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፤ የውጭ ምንዛሬ ለማስገኘትና የስራ ዕድል ለመፍጠር እገዛ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዓለም ባንክ ግሩፕ የግብርናና ምግብ ዓለም አቀፍ ተሞክሮ ዳይሬክተር ዶክተር ማርቲ ቫን ኒውኮፕ፤ ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል የሚያስችሉ አስደናቂ ውጤቶችን ማስመዝገቧን ገልጸዋል፡፡ የዓለም አቀፍ ግጭቶች፣ የማክሮ ኢኮኖሚ አለመረጋጋት የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እንቅፋት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ መሰል ችግሮች ሲያጋጥሙ ሀገራት በትብብር መስራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል፡፡ የዓለም ባንክ በዝቅተኛ እርሻ ላይ የተሰማሩ አርሶ አደሮች በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚደርስባቸውን ተጽዕኖ ለመቀነስ 1 ነጥብ 5 ቢሊየን ዶላር ድጋፍ ያደርጋል ሲሉ አረጋግጠዋል። የግብርና ሚኒቴርና የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ከዓለም አቀፍ የግብርና ምርምር ማዕከላት ጥምረት ጋር በመተባበር አውደ ጥናቱ መዘጋጀቱ ታውቋል።
በኦሮሚያ ክልል ለዘንድሮው ዓመት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ4 ቢሊዮን በላይ ችግኝ ተዘጋጅቷል - የክልሉ ግብርና ቢሮ
May 25, 2023 120
አዲስ አበባ ግንቦት 17/2015 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ለዘንድሮው ዓመት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ4 ቢሊዮን በላይ ችግኝ መዘጋጀቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኤሊያስ ከድር፤ በ4ኛው ዙር የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የኦሮሚያ ክልል ከ4 ቢሊዮን በላይ ችግኞች መተከላቸውን ነው የተናገሩት፡፡ በአጠቃላይ በአረንጓዴ አሻራ የተተከሉ ችግኞች የአካባቢን ሚዛን በመጠበቅ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራን በማሻሻል ከፍተኛ ሚና እየተጫወቱ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ለዘንድሮው ዓመት አረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብርም በክልሉ 4 ነጥብ 9 ቢሊዮን ችግኞች መዘጋጀታቸውን ጠቅሰው፤ በዋናነት ለፍራፍሬ ችግኞች ትኩረት በመስጠት የችግኝ ማፍላት ስራ ሲከናወን መቆየቱን ተናግረዋል። ለችግኝ ተከላ የሚሆን ቦታ መረጣና ጉድጓድ ዝግጅትም ቀደም ብሎ መጀመሩን ገልጸዋል፡፡ ባለፉት አራት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በክልሉ 13 ነጥብ 6 ቢሊዮን ችግኞች መተከላቸውን ጠቅሰው፤ የጽድቀት መጠናቸውንም 88 ነጥብ 6 በመቶ ማድረስ እንደተቻለ ተናግረዋል። ከሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በበጋው ወቅት 6 ሺህ 450 ተፋሰስ ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መከናወኑንም ጨምረው ገልጸዋል። በተጨማሪም ከ500 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ የተራቆተ አከባቢ ከንክኪ ነጻ ማድረግ መቻሉንም ነው የተናገሩት፡፡ በክልል ደረጃ ከሰኔ 15 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብሩ እንደሚካሄድ ጠቁመው፤ ለዚህም በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎችን በበጎ ፈቃድ ለማሳተፍ ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን ተናግረዋል። በዘንድሮው ዓመት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በአገር ዓቀፍ ደረጃ 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ዝግጅት በመካሄድ ላይ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ማሳወቃቸው ይታወሳል።
በምስራቅ ሸዋ ዞን የቆላ የፍራፍሬ ዛፎች ለመትከል ዝግጅት ተጠናቋል - የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት
May 25, 2023 123
አዳማ ግንቦት 17/2015 (ኢዜአ) በመጪው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለደን አገልግሎት ከሚውሉ ችግኞች በተጨማሪ በቆላማ የዞኑ አካባቢዎች የፍራፍሬ ዛፎች ለመትከል ዝግጅት እየተጠናቀቀ መሆኑን የምስራቅ ሸዋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ መስፍን ተሾመ እንደገለጹት በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በዞኑ ከ200 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ አገልግሎት የሚሰጡ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተጠናቀቀ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚሁ ጋር በዞኑ ቆላማ አካባቢዎች ፍራፍሬ ዛፎች ለመትከል የችግኝ ዝግጅት መጠናቀቁን ገልጸው፤ በአሁኑ ወቅት በ11 የዞኑ ወረዳዎች የጉድጓድ ዝግጅት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የቴምር፣ ዘይቱና፣ ግሽጣ፣ አቮካዶ እንዲሁም የቀርካሃ ችግኞች መዘጋጀታቸውን የገለጹት ሃላፊው ከመጪው ወር ጀምሮ ወደ ተከላ ለመግባት የቅድመ ዝግጅት ስራ እያከናወኑ መሆኑን አመልክተዋል። ለእቅዱ ስኬታማነትም በ52 የችግኝ ጣቢያዎች ዘርፈ ብዙ አገልግሎትና ጥቅም የሚሰጡ ችግኞች መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል። አምና በዞኑ ከተተከሉት ውስጥ ከ90 በመቶ በላይ መፅደቃቸውን ጠቅሰው ከዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ፕሮግራም ጎን ለጎን ለተተከሉት ሰፊ የእንክብካቤ ስራ መከናወኑን ጠቅሰዋል። የተራቆቱ መሬቶችን ከሰውና እንስሳት ንክኪ ነፃ በማድረግ ረገድ በዘንድሮ ዓመት 500ሺህ ሄክታር ለማካለል እየተሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ይህም ለስራ አጥ ወጣቶች አማራጭ የስራ እድል እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ባለፈው ዓመት 38 ሺህ ለሚሆኑት ዜጎች በችግኝ ዝግጅት እንዲሁም ከደንና ከደን ውጤቶች ጋር በተያያዘ የስራ እድል መፈጠሩን ጠቅሰው ዘንድሮ ደግሞ 60ሺህ ለሚሆኑት ዜጎች በዚህ ዘርፍ የስራ እድል ለመፍጠር አቅደው እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰዋል። በእስከ አሁኑ ሂደት ከ45ሺህ በላይ ለሚሆኑት ወጣቶችና ሴቶች የስራ እድል በዘርፉ መፈጠሩን ሃላፊው አክለዋል።