አካባቢ ጥበቃ
በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችንና ስነ ምህዳርን መሰረት ያደረገ ተከላ ለማካሄድ ዝግጅት ተደርጓል
Jun 14, 2025 53
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችንና ስነ ምህዳርን መሰረት ያደረገ ተከላ ለማካሄድ ዝግጅት መደረጉ ተገለጸ። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈፃሚ ፋኖሴ መኮንን ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው ክረምት ለሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በቂ ዝግጅት ተደርጓል። በመርሃ ግብሩ 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ መትከል የሚያስችል ዝግጅት መደረጉን ገልጸው፤ ለሀገር በቀልና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ላላቸው ችግኞች ትኩረት መሰጠቱንም ጠቁመዋል።   የችግኝ ተከላ ሂደቱም ስነ-ምህዳርን መሰረት ያደረገ እንደሚሆን ጠቅሰው፤ ለዚህም አስፈላጊ የሆኑ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸዋል። ባለፉት አመታት ከተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሮች ዘርፈ ብዙ ትሩፋቶች መገኘታቸውን ያነሱት መሪ ስራ አስፈጻሚው ይህም አሁን ላይ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚደረገው ርብርብ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እና የስራ ዕድል መፍጠር መቻሉን ተናግረዋል።   የጉለሌ እጽዋት ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ጉተማ ሞረዳ በበኩላቸው፤ አዲስ አበባ ከተማን ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የአረንጓዴ አካባቢ ሽፋንን ማሳደግ ወሳኝ ነው። ይህም የአየር ብክለትን ለመከላከል ጉልህ ሚና እንዳለው አንስተው፤ ለዚህም ሀገር በቀል እጽዋት ተመራጭ መሆናቸውን ተናግረዋል። ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብርም በማዕከሉ ከተዘጋጁት ችግኞች 50 በመቶ የሚሆኑት ሀገር በቀል ዝርያ ያላቸው ናቸው ብለዋል።    
የሸገር ከተማ የመኖሪያ ብቻ ሳይሆን የማምረቻ ከተማ እንዲሆን በተከናወኑ ስራዎች ውጤት እየተገኘ ነው - ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር)
Jun 12, 2025 101
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፡- የሸገር ከተማ የመኖሪያ ብቻ ሳይሆን የማምረቻ ከተማ እንዲሆን በተከናወኑ ስራዎች ውጤት እየተገኘ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር) ተናገሩ። በሸገር ከተማ አስተዳደር መነ አቢቹ ክፍለ ከተማ የአፕል ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር የአስተዳደሩ አመራሮች፣ የአገር መከላከያ ሰራዊት አባላት እና ነዋሪዎች በተገኙበት ተካሄዷል።   በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት ከንቲባ ተሾመ አዱኛ (ዶ/ር)፣ ከተማው ከተመሰረተ ጀምሮ የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ከተማዋ የመኖሪያ ብቻ ሳትሆን የማምረቻ ማዕከል እንድትሆን ዘርፈ ብዙ ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል። ከተማውን የዘመናዊ ግብርና ማዕከል ለማድረግ ባለፉት ዓመታት ከ10 ሺህ በላይ የማምረቻ ሼዶች ተገንብተው ለበርካታ ሰዎች የስራ እድል መፈጠሩን ገልጸዋል። በሼዶቹ ውስጥ ሰፋፊ የዶሮ እርባታ ስራዎች፣ የወተት ላሞች እርባታ፣ በስጋ እንስሳት ማድለብና በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ውጤታማ ስራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በተያዘው ክረምትም በከተማ አስተዳደሩ በ1 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ የአፕልና አቮካዶ ችግኝ እንደሚተከል ገልጸው ዛሬም በመነ አቢቹ ክፍለ ከተማ በ38 ሄክታር መሬት ላይ የአፕል ችግኝ መተከሉን ተናግረዋል።   የሸገር ከተማ ምክትል ከንቲባ እና የግብርና ክላስተር አስተባባሪ አቶ ግርማ ሀይሉ፣ በከተማ አስተዳደሩ ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። በዚህ ክረምትም የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያግዝና ለውጭ ገበያ የሚውሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች ይተከላሉ ብለዋል። ከሚተከሉት የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች መካከል ከ50 በመቶ በላይ የሚሆነው የአፕል ችግኝ መሆኑንም ጨምረው ገልጸዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የሸገር ከተማ አስተዳደር መነ አቢቹ ክፍለ ከተማ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፍቃዱ ሆርዶፋ በበኩላቸው በክፍለ ከተማው በዚህ ክረምት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል አስፈላጊ ዝግጅቶች መደረጋቸውን ተናግረዋል። በክፍለ ከተማው በአጠቃላይ በ50 ሄክታር መሬት ላይ ከ50 ሺህ በላይ የአፕል ችግኝ ተከላ መጀመሩን ገልጸው የአካባቢው አርሶ አደርም መልካም ተሞክሮ እየወሰደ የተተከለውን ችግኝ እንዲንከባከብም አሳስበዋል።   በችግኝ ተከላው ላይ ከተሳተፉ የአካባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ መስፍን መላኩ፣ በክረምቱ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።   በተከላው ተሳትፎ ያደረጉት የአፕል ችግኝ ጠቀሜታው ትልቅ መሆኑን በመገንዘብ መሆኑን ተናግረው በአካባቢው የአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ሊጠናከር እንደሚገባም አመልክተዋል።    
በሚቀጥሉት አሥር ቀናት በተለይም በምዕራብ አጋማሽ የሀገሪቱ ክፍሎች የተሻለ ርጥበት ይኖራቸዋል - ኢንስቲትዩቱ
Jun 12, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አሥር ቀናት በተለይም በምዕራብ አጋማሽ የሀገሪቱ ክፍሎች የተሻለ የርጥበት ሁኔታ እንደሚኖራቸው የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የሚኖረውን የአየር ትንበያ አስመልክቶ ለኢዜአ በላከው መግለጫ በሚቀጥሉት ቀናት የሚኖረው የአየር ሁኔታ ለእርሻ ስራ እንቅስቃሴ በአመዛኙ አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው አመላክቷል። ከዚህም ጋር ተያይዞ በምዕራብ እና በሰሜን ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚጠበቀው ከባድ ዝናብ ለወቅቱ የእርሻ ስራ እንቅስቃሴ በአመዛኙ አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረውም ጠቁሟል። ሆኖም ሊኖሩ የሚችሉ ተያያዥ ስጋቶችን ለመቀነስና የሚኖሩትን መልካም አጋጣሚዎች ለመጠቀም የቀረቡትን የግብርና ሚቲዎሮሎጂ ምክረ ሀሳቦች በሁሉም ደረጃ በተገቢው ሁኔታ መተግበር እንደሚያስፈልግ ተጠቁሟል። በቀጣዮቹ ቀናት የሚኖረውን የአየር ሁኔታ የተመለከተው ትንበያ ለክረምት ዝናብ መፈጠር አስተዋጽኦ የሚያደርጉ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች ከቀን ወደ ቀን እየተስፋፉና እየተጠናከሩ እንደሚሄዱ ያሳያል ነው ያሉው። ከዚሁ ጋር በተያያዘም፣ በምዕራብ አጋማሽ የሀገሪቱ ክፍሎች ላይ የተሻለ የዝናብ መጠንና ሥርጭት እንደሚኖራቸው የትንበያ መረጃዎች ይጠቁማሉ ሲልም ገልጿል። በዚህም ርጥበታማው የአየር ሁኔታ በተለይም በደቡብ ምዕራብ፣ በምዕራብ፣ በሰሜን ምዕራብና በመካከለኛዉ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ በመጠንም ሆነ በሥርጭት እየተስፋፋ ከመሄዱ ጋር ተያይዞ ብዙ ቦታዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖራቸው ተጠቁሟል። ጥቂት ስፍራዎቸ ላይ ደግሞ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖር አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች አመላክተዋል ነው ያለው። በሚቀጥሉት ቀናቶች ከሚጠናከሩት የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች ላይ በመነሳት የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የሀገሪቱ አካባቢዎች ብዙ ቦታዎቻቸውን የሚሸፍን ከቀላል እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ነው መረጃው ማመላከቱንም አስታውቋል። በተጨማሪም አልፎ አልፎ በውሃ አካላትና በካባቢ አየር ውስጥ ከሚጠናከሩት የሚቲዎሮሎጂ ገጽ ላይ በመነሳት በምዕራብ እና በሰሜን ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች በ24 ሠዓት ውስጥ ከ30 ሚሜ በላይ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች አመላክተዋል ብሏል። በቀጣይ አስር ቀናት የክረምት ወቅት መጀመሩን ተከትሎ በአብዛኛው ርጥበት ተጠቃሚ በሆኑ ተፋሰሶች ላይ ከመጠነኛ እስከ ከፍተኛ የሆነ የገፀ ምድር የውሃ ፍሰት እንደሚኖራቸው ይጠበቃል ሲልም ገልጿል። የሚኖረውን አዎንታዊ የርጥበት ሁኔታ በአግባቡ ለመጠቀምና አሉታዊ ሁኔታን ለመቀነስ የውሃ ማንጣፈፍያ እና የጎርፍ መቀልበሻ ቦዮችን ማዘጋጀት እንደሚገባም ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል።
ብርቅዬ የዱር እንስሳትና ዕጽዋትን ከህገ ወጥ አደንና ዝውውር የመጠበቅ ተግባርን አጠናክሮ መቀጠል ይገባል - ሚኒስቴሩ
Jun 9, 2025 142
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 2/2017(ኢዜአ)፦ በብሔራዊ ፓርኮች ውስጥ የሚገኙ ብርቅዬ የዱር እንስሳትና ዕጽዋትን ከህገ ወጥ አደንና ዝውውር የመጠበቅ ተግባርን አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባ የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ስለሺ ግርማ ገለጹ። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን ሕገ-ወጥ የዱር እንስሳት ዝውውርን ለመቆጣጠር ከዛሬ ጀምሮ ለሚቀጥሉት አምስት ቀናት የሚቆይ የባለድርሻ አካላት ስልጠና በአዲስ አበባ አስጀምሯል። በስልጠናው የአየር መንገድ ተቆጣጣሪ አካላት፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ የጉምሩክ ኮሚሽን ተወካዮች፣ ኢንተርፖል፣ የአቬዬሽንና ሌሎች ተቋማት ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ። የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ስለሺ ግርማ በዚሁ ወቅት፤ ስልጠናው ሕገ-ወጥ የዱር እንስሳትና ዕፅዋት ዝውውርን መቆጣጠር እንዲቻል ግንዛቤ በመፍጠር ጉልህ ፋይዳ እንደሚያበረክት ገልጸዋል። የፀጥታ እና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት የዱር እንስሳትና ዕፅዋትን ከህገ ወጥ አደንና ዝውውር የመጠበቅ ተግባርን አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባ ጠይቀዋል። በዚህም ብሔራዊ የዱር እንስሳትና ዕፅዋት ጥበቃ ፓርኮችና የማህበረሰብ ጥብቅ የደን ስፍራዎች ለቱሪዝም ኢኮኖሚያዊ አቅም እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ ብርቅዬ የዱር እንስሳት በሚገኙባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ዜጎችን በማሳተፍ የአትክልትና ፍራፍሬ እና ሀገር በቀል ዕፅዋት ልማትን ጨምሮ የኢኮ ቱሪዝም ጥበቃ ልማት ላይ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ፤ ስልጠናው ሕገ-ወጥ የዱር እንስሳት ዝውውርን ለመቆጣጠርና በትብብር ለመስራት ያለመ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ፣ በአፍሪካ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ ህገ-ወጥ የዱር እንስሳት ዝውውር ዓይነቱንና ቅርጹን እየቀያየረ እንደሚፈጸም ገልጸዋል። ስልጠናው ሕገ-ወጥ የዱር እንስሳት አደንና ዝውውር ወንጀሎችን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት የባለድርሻ አካላትን ሚና ለማሳደግ ጉልህ ጠቀሜታ እንደሚኖረውም አስረድተዋል።
አዋጁ ከተሞችን ከብክለት የጸዱ ምቹና ለኑሮ ተስማሚ ማድረግ የሚያስችል ነው - ባለስልጣኑ
Jun 9, 2025 393
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 2/2017(ኢዜአ)፦ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ከተሞችን ከብክለት የጸዱ ምቹና ለኑሮ ተስማሚ ማድረግ የሚያስችል መሆኑን የኢፌዴሪ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ፡፡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ግንቦት 26 ቀን 2017 ዓ.ም ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 ሥራ ላይ እንዲውል ማጽደቁ ይታወቃል፡፡ አዋጁ የአየር፣ የውሃና የአፈር ብክለትን ለመቀነስና የዜጎች ጤንነትን ለመጠበቅ የጎላ አበርክቶ ያለው ነው፡፡   በባለስልጣኑ የከተማ ቆሻሻ አያያዝና ክትትል ዴስክ ኃላፊ ዋሲሁን ዓለሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ የከተሜነት መስፋፋትን ተከተሎ የህዝብ ቁጥር በመጨመሩ የአኗኗር ዘይቤው ተለውጧል፡፡ በዚህም ነባሩ አዋጅ ቁጥር 513/1999 የከተሞችን የቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ስርዓት መልክ ለማስያዝ ውስንነቶች ስላሉበት በአዋጅ ቁጥር 1383/2017 እንዲተካ ተደርጓል ብለዋል። ከተሞች ጽዱና ለኑሮ ተስማሚ እንዲሆኑ የቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ስርዓት ምን መምሰል አለበት የሚለውን ለመቆጣጠርና ለመከታተል ይቸገሩ እንደነበር ገልጸዋል። ነባሩ አዋጅ ግለሰቦች፣ ማህበራትና ድርጅቶች የሚያመነጩትን ቆሻሻ መቀነስ አልያም በአግባቡ ማስወገድ ወይም በድጋሚ ጥቅም ላይ ማዋል የሚችሉበትን መንገድ በግልጽ ያስቀመጠ አልነበረም ብለዋል፡፡ በቅርቡ የጸደቀው አዋጅ ግለሰቦች ከመኖሪያ ቤታቸው 20 ሜትር፣ አገልግሎት ሰጭ ተቋማትና የንግድ ድርጅቶች ደግሞ 50 ሜትር ዙሪያ እንዲያጸዱ ያስገድዳል ነው ያሉት፡፡ ያመነጩትን ቆሻሻ በዘፈቀደ መጣል ወይም ማስወገድ አይቻልም ያሉት ኃላፊው፤ ከተማ አስተዳደሩ በሚለያቸው ስፍራዎች አልያም ፈቃድ ለተሰጣቸው ቆሻሻ ሰብሳቢዎች ማስረከብ እንዳለባቸውም ጠቁመዋል፡፡   በባለስልጣኑ የአካባቢ ህጎችና ደረጃዎች ዴስክ ኃላፊ ወንደሰን ታደሰ በኢትዮጵያ የፕላስቲክ ምርቶችን የመጠቀም ባህል በእጅጉ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ የተሻሻለው አዋጅ በተለየ ሁኔታ እንዳይመረቱና ጥቅም ላይ እንዳይውሉ ክልከላ ያደረገው ለአንድ ጊዜ ብቻ አገልግሎት ላይ በሚውሉ የፕላስቲክ ከረጢቶች በተለምዶ "ፔስታል" በሚባሉት ምርቶች ላይ ብቻ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በፕላስቲክ ከረጢት ላይ የተለየ ክልከላ የተደረገው በአካባቢ ብክለትና በማህበረሰብ ጤና ላይ የሚያደርሱትን ጉዳት ታሳቢ በማድረግ ነው ብለዋል፡፡ በነባሩ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ስፋታቸው ከ0 ነጥብ 03 ሚሊ ሜትር በታች የሆኑ የፕላስቲክ ከረጢቶችን ማምረት ይቻል እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ በባለስልጣኑ የከተማ ቆሻሻ አያያዝና ክትትል ዴስክ ኃላፊ ዋሲሁን ዓለሙ እንዳብራሩት ፌስታሎቹ በቀላሉ የሚመረቱ በመሆናቸው ማን የት እንዳመረታቸው ለመቆጣጠርና ርምጃ ለመውሰድ አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡ በዚህም ከ11 በመቶ የማይበልጠው የፕላስቲክ አጠቃቀም በአሁኑ ወቅት ከ400 በመቶ በላይ ዕድገት ማሳየቱን ጠቅሰው፤ የፕላስቲክ ከረጢቶች ሙሉ በሙሉ እንዳይመረቱ ክልከላ ማድረግ የተሻለ አማራጭ ሆኖ መገኘቱን ገልጸዋል፡፡ የፕላስቲክ ከረጢቶችን ማምረትና መጠቀም አዋጁ በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ ባሉት ስድስት ወራት ተፈፃሚ እንደማይሆን የገለጹት ደግሞ የአካባቢ ህጎችና ደረጃዎች ዴስክ ኃላፊ ወንደሰን ታደሰ ናቸው፡፡   በቀጣዩ ስድስት ወራት ሙሉ ክልከላ የተደረገባቸው እንዲሁም በከፊል ሊፈቀዱ የሚችሉት የፕላስቲክ አይነቶች የትኞቹ እንደሆኑ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ ይከናወናል ብለዋል፡፡ ይህም በዘርፉ የተሰማሩ አምራቾችና ከውጭ የሚያስገቡ ነጋዴዎች ወደ ሌላ ዘርፍ ሽግግር የሚያደርጉበት ጊዜ እንዲኖራቸው ታሳቢ ተደርጎ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከስድስት ወር በኋላ በደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 የተቀመጡ ግዴታዎች ተግባራዊ እንደሚደረጉም አረጋግጠዋል። በባለስልጣኑ የከተማ ቆሻሻ አያያዝና ክትትል ዴስክ ኃላፊ ዋሲሁን ዓለሙ፤ የከተማ አስተዳደሮች ከግለሰብ ጀምሮ እስከ ተቋማት ተዘዋውረው ቆሻሻ መሰብሰብ ለሚችሉ ማህበራት ፈቃድ እንደሚሰጡ ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም የከተማ አስተዳደሮች ቆሻሻ ለመሰብሰብ የሚጠበቅበትን ክፍያ መክፈሉን፣ ቆሻሻውን ፈቃድ ለተሰጣቸው አካላት ማስረከቡን ይከታተላል፤ ይቆጣጠራል ብለዋል፡፡ ከዚህም ባለፈ በአዋጁ የተቀመጡ ድንጋጌዎችን አልፈው የተገኙ አካላት የከተማ አስተዳደሮች በሚያወጡት መመሪያ መሰረት በአስተዳደራዊ ህጎች በወንጀል ተጠያቂ ይሆናሉ ነው ያሉት፡፡
በጉጂ ዞን የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቋቋም በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ስራዎች ለውጥ እየታየ ነው
Jun 7, 2025 132
ነገሌ ቦረና፣ግንቦት 30/2017(ኢዜአ)፦በጉጂ ዞን ባለፉት አመታት የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቋቋም በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በተሰራ ስራ ለውጥ እየታየ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ወንዶ ሸርቦቴ፤ በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተለያዩ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በ22 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ መተከላቸውን ገልጸዋል። የተተከሉ ችግኞችም በህዝብ ተሳትፎ እንክብካቤና ጥበቃ ተደርጎ በስፋት መጽደቅ ማስቻሉን ተናግረዋል። ከተተከሉት ችግኞች የደን፣ የጥላ ዛፍ፣ የእንስሳት መኖና የፍራፍሬ ችግኞች ዋና ዋናዎቹ እንደሆኑም ለአብነት አንስተዋል፡፡ ድርቅና የአካባቢ መራቆትን በዘላቂ ልማት ለመቋቋም በተመሳሳይ በዘንድሮም ከ87 ሚሊዮን በላይ ችግኝ ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል፡፡ ለዚህም በ13ቱም ወረዳዎች በተፈጥሮና በሰው ሰራሽ ምክንያት የተራቆተ ከ20 ሺህ ሄክታር በላይ የችግኝ መትከያ መሬት መዘጋጀቱን ገልጸዋል፡፡ በጽህፈት ቤቱ የደን አስተዳደር ቡድን መሪ አቶ ቴድሮስ ገብሬ፤ ለአረንጓዴ አሻራ የተሰጠው ትኩረት የአካባቢ መራቆትን እየታደገ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በዞኑ በተሰራው ስራ ምንጮች እየጎለበቱ ከአመት አመት እየፈሰሱ እንደሆነና መጠለያ አጥተው የተሰደዱ የዱር እንስሳት ጭምር እየተመለሱ መሆኑን ተናግረዋል። በዞኑ ከ6 አመታት በፊት ከ274 ሺህ ሄክታር በታች የነበረው የዞኑ ደን ሽፋንም ወደ 382 ሺህ ሄክታር ከፍ ማለቱን ጠቅሰዋል፡፡ ችግኝ ከመትከል ጎን ለጎን የዞኑ ህዝብ ተሳትፎ ድጋፍና ትብብር ለደን ልማት ሽፋኑ መጨመር ከፍተኛ ድርሻ ማበርከቱንም ነው የተናገሩት፡፡
የቢሾፍቱ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ‘ስማርት ሲቲ' ጽንሰ ሀሳብ እውን በሚያደርግ መልኩ እየተከናወነ ነው
Jun 7, 2025 114
ቢሾፍቱ፤ግንቦት 30/2017(ኢዜአ)፦የቢሾፍቱ ከተማ የኮሪደር ልማት የከተማዋን ‘ስማርት ሲቲ'ጽንሰ ሀሳብ እውን በሚያደርግ እና የቱሪስት ማዕከልነትን ታሳቢ ባደረገ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን የከተማው ማዘጋጃ ቤት አስታወቀ። የቢሾፍቱ ከተማ አስተዳደር ባለፈው ዓመት በሪጂኦፖሊታንት ደረጃ መዋቀሯ የሚታወስ ሲሆን የኮሪደር ልማት ስራም በተሻለ መልኩ እየተከናወነባቸው ካሉ ከተሞች መካከል መሆኗ ተጠቅሷል። የከተማ አስተዳደሩ ማዘጋጃ ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ ገብሬ ዳቢ ለኢዜአ እንዳሉት፥ የከተማው የኮሪደር ልማት ስራ በልዩ ኢኒሺዬቲቭ እየተከናወነ ይገኛል። የከተማ አስተዳደሩ ስራውን ከመጀመሩ በፊት ለአመራሩ፣ለነዋሪው እና ለባለድርሻ አካላት በልማት ስራው ዙሪያ በቂ ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ ተከናውኖ ወደ ስራ መገባቱን ተናግረዋል። ለኮሪደር ልማቱ የግለሰብ፣የመንግስትና የንግድ ቤቶችን ከማፍረስ ባለፈ የመብራት፣ የቴሌኮምና የውኃ መስመሮችን በጥንቃቄ የማንሳት ስራው በተቀናጀ አግባብ ሲከናወን መቆየቱን ገልጸዋል። የኮሪደር ልማቱ በውስጡ የ24 ኪሎ ሜትር የአስፈልት መንገድ፣ ዘመናዊ የፍሳሽ ማስወገጃ ቦዮች፣ የመንገድ ዳርቻ ማስዋብና የአረንጓዴ ስፍራዎች፣ የሳይክልና እና የእግረኛ መንገድን ያካተተ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም የመብራት፣የቴሌኮም እና የደህንነት ካሜራ በዘመናዊ መንገድ ከኮሪደር ልማቱ ጋር ተጣጥመው እንዲዘረጉ እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል። የቢሾፍቱ ከተማ የኮሪደር ልማት ስራ በዋናነት የከተማዋን ‘ስማርት ሲቲ’ ጽንሰ ሀሳብ እውን በሚያደርግ እና የቱሪስት ማዕከልነትን ታሳቢ ባደረገ መልኩ የሚከናወን በመሆኑ ስራውም በዚሁ አግባብ እየተፋጠነ ይገኛል ብለዋል። ቢሾፍቱ በተፈጥሮ የታደለችና የሰባት ሀይቆች ባለቤት መሆኗን አስታውሰ፥ የኮሪደር ልማት ስራው ከተማዋ በተፈጥሮ በታደለችው መስህብ ላይ ተጨማሪ ውበት በሚጨምር መልኩ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። አፈጻጸሙም በታቀደው መሰረት እየተከናወነ መሆኑን ያነሱት ስራ አስኪያጁ የከተማው ነዋሪ፣ባለሀብቶችና ባለድርሻ አካላት ሰፊ ተሳትፎ ማድረጋቸውን አክለዋል። የከተማው የኮሪደር ልማት ስራ በአማካሪነት የሚከታተለው ድርጅት ምክትል ተጠሪ መሀንዲስ ክበበ በየነ፣ በእስካሁኑ ሂደት የኮሪደር ልማት ስራው 65 በመቶ መከናወኑን አስረድተዋል። ከአስፋልት መንገድ ባሻገር አምስት ሜትር የእግረኛ፣ ሶስት ሜትር የሳይክል መንገድ፣ በመሬት ውስጥ የሚዘረጋ የኤሌክትሪክ መስመር እና 'ስማርት ፖል' ያካተተ የኮሪደር ልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በከተማው ዳካ ቦራ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት አቶ ገቢ ዋሪዮ፣ ''በኮሪደር ልማቱ መንገድ እንዲሰፋ እየተደረገ ነው፣ ከተማው እየታደሰ በመሆኑ ስራውን እየደገፍን ነው'' ብለዋል። በተለይም እየተገነቡ የሚገኙ የአረንጓዴ ስፍራዎች ነዋሪው ንጹህ አየር የሚያገኝበት እና ሌሎች ማህበራዊ ጉዳዮችን የሚፈጽምበት በመሆኑ ስራው ትልቅ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ጠቅሰዋል። በኮሪደር ልማቱ ተጨማሪ የአስፋልት መንገድን ጨምሮ የእግርኛ መንገዶች እየተገነቡ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ በከተማው የዱከም ክፍለ ከተማ ነዋሪው አቶ ሚኒሻ ደጀኔ ናቸው። የኮሪደር ልማት ስራው እንዲፋጠን አስፈለጊውን ድጋፍ ማድረጋቸውን እንደሚቀጥሉም ተናግረዋል። ተማሪ ሴና ካሳሁን በበኩሏ፥ በኮሪደር ልማት ሰራው ምክንያት የተሰራው መለስተኛ ፓርክ ለነዋሪው ማረፊያ መሆኑን ጠቅሳ፥ የአካባቢውን ውበትም እየጨመረ መምጣቱን ተናግራለች።
በክልሉ የፕላስቲክ ምርትን በአግባቡ በመጠቀም የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል የተቀናጀ ተግባር እየተከናወነ ነው
Jun 5, 2025 117
ባህር ዳር / ደሴ ፤ ግንቦት 28/2017 (ኢዜአ) ፡-በአማራ ክልል የፕላስቲክ ምርትን በአግባቡ በመጠቀም የአካባቢ ብክለትን ለመከላከልና ብዝሃ ህይወትን ለመጠበቅ የተቀናጀ ተግባር እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ የአካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ። "የፕላስቲክ ብክለት ያብቃ" በሚል መሪ ሃሳብ የዓለም የአካባቢ ቀን በክልል ደረጃ ዛሬ ተከብሯል። የክልሉ የአካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ኃላፊ አቶ በልስቲ ፈጠነ በመድረኩ እንደገለጹት፤ በየአካባቢው በዘፈቀደ የሚጣሉ የፕላስቲክ ቆሻሻዎች የአካባቢን ስነ-ምህዳር እየጎዱ ናቸው።   የፕላስቲክ ምርትን የምንጠቀምበት አግባብ የአካባቢ ብክለትን በማስከተሉ ለብዝሃ ህይወት መመናመን መንስኤ እየሆነ መጥቷል ብለዋል። ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ፕላስቲኮች አካባቢን እንዳይበክሉ ተሰብስበው መልሰው ጥቅም ላይ የሚውሉበትን አቅም ይበልጥ ለማጠናከር ከአጋር አካላት ጋር እየሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል። ችግሩን ለመፍታት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ከሚከናወነው የግንዛቤ ፈጠራ ስራዎች ባለፈ ህጋዊ እርምጃ እየተወሰደ መሆኑን ተናግረዋል። ከመረሃ ግብሩ ተሳታፊዎች መካከል በባህርዳር ከተማ የሚገኘው አይቸው፣ ሜሮንና ጓደኞቹ የሀይላንድ መልሶ መጠቀም የህብረት ስራ ማህበር ሰብሳቢ አቶ አይቸው ደባስ እንዳለው፤ የወዳደቁ የውሃ መያዣ ፕላስቲኮችን ከሰብሳቢዎች በመረከብ ፈጭተው ለፋብሪካዎች እያስረከቡ ነው። በተመሳሳይ "የፕላስቲክ ብክለትን እንግታ" በሚል መሪ ሀሳብ የፓናል ውይይት በደሴ ከተማ ተካሂዷል።   የደሴ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ሽመልስ ጌታቸው በወቅቱ እንደገለጹት ፤ ከተማዋን ጽዱ፣ ውብ ለማድረግ ከህብረተሰቡ ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው፡፡ የቆሻሻ አወጋገድ ስርዓቱን ለማዘመን የፈሳሽና የደረቅ ቆሻሻ ማስወገጃ እየተገነባ መሆኑን ጠቁመው ፤ የኮሪደር ልማትም ይህን ለማሳካት አጋዥ መሆኑን አክለዋል። ሕብረተሰቡ ፕላስቲክ የሚያደርሰውን የአካባቢ ብክለት በመገንዘብ ችግሩን ለመከላከልና ከተማችንን ጽዱና ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ የሚደረገውን ጥረት ሊደግፍ ይገባል ያሉት ደግሞ የደሴ ከተማ አስተዳደር አካባቢ ጥበቃ፣ ጽዳትና ውበት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ዮናስ ሰይድ ናቸው። ሁሉም የሚጠቀመውን የፕላስቲክና ሌሎች ቆሻሻዎች በከተማው በተለያዩ አካባቢዎች በተቀመጡ የቆሻሻ ማስቀመጫ ሥፍራዎች ላይ ሊያስቀምጥ ይገባልም ብለዋል፡፡ ከፓናል ውይይቱ ተሳታፊዎች ውስጥ አቶ ቢላል መሀመድ በሰጡት አስተያየት ፤ አካባቢያችንን ሰላም በመጠበቅ ከተማችንን ጽዱና ውብ ለማድረግ የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ ገልጸዋል፡፡
የአየር ንብረት ለውጥን ተከትሎ የሚመጡ ችግሮችን ለመከላከል የዘርፉ ምሁራን ሚና ሊጠናከር ይገባል
Jun 5, 2025 101
ነቀምቴ፤ ግንቦት 29/2017(ኢዜአ)፡- የአየር ንብረት ለውጥን ተከትሎ የሚመጡ ችግሮችን ለመከላከል የዘርፉ ምሁራን ሚና ሊጠናከር እንደሚገባ ተጠቆመ። በወለጋ ዩኒቨርሲቲ የተለያዩ የመንግስት እና የግል ድርጅት አመራሮች የተሳተፉበት የአለም የአየር ንብረት ቀን በፓናል ውይይት ተከብሯል። በወለጋ ዩኒቨርሲቲ የምርምር እና የቴክኖሎጂ ሽግግር ዘርፍ ምክትል ፕሬዚዳንት ዲሪባ ዲባ (ዶ/ር ) በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት የአየር ንብረት ለውጥ የአለም መንግስታት ትልቅ መነጋገሪያ ነው። በኢትዮጵያም የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ በተለያየ መልኩ እየተከሰተ ጉዳቶችን እያስከተለ መሆኑን ተናግረው መንግስትም የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን ለመመከት የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን እያደረገ ይገኛል ብለዋል።   የመንግስት ጥረት የበለጠ ውጤት እንዲያመጣ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የሚገኙ የዘርፉ ምሁራን ሙያዊ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባ አመልክተዋል። በተለይም ባላቸው እውቀት እና ልምድ በመታገዝ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን ለመከላከል የሚያግዙ ጥናቶችን በማካሄድ መፍትሄ ጠቋሚ ሀሳቦችን ማፍለቅ መቻል እንዳለባቸውም አክለዋል። በመድረኩ ላይ የውይይት መነሻ ጽሁፍ ያቀረቡት በዩኒቨርሲቲው መምህር ቶሌራ መርጋ (ዶ/ር)፤ ''የአየር ንብረት ጉዳይ የሰው ልጅ የመኖር እና ያለመኖር ጉዳይ በመሆኑ ትኩረት ይሻል'' ብለዋል። በተለይም የአካባቢ ብክለትን ከሚያባብሱ ችግሮች መካከል የፕላስቲክ ቁሳቁሶችን ያለአግባብ መጠቀም አንዱ መሆኑን ጠቅሰው የፕላስቲክ ውጤቶች አወጋገድ ስርዓትን በትኩረት መተግበር እንዳለበትም አመልክተዋል። ከዚህ ጎን ለጎን የአካባቢ ስነ-ምህዳርን ለመጠበቅ የሚደረገው ጥረት የበለጠ ውጤታማ እንዲሆን ሁሉም የበኩሉን አስተዋጽኦ ማበርከት እንዳለበትም አስረድተዋል። የነቀምቴ ከተማ የአካባቢ ጥበቃ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ብርሀኑ አሰፋ በበኩላቸው ከአካባቢ ጥበቃ ጋር በተያያዘ የህብረተሰቡን ግንዛቤ ለማሳደግ ምሁራን ሚናቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው ተናግረዋል። የከተማዋን ፅዳት ለመጠበቅ እና የፕላስቲክ ቁሶችን መልሶ መጠቀም ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረው ለዚሁ ተግባርም ወጣቶችን በማደራጀት ወደ ስራ ለማስገባት ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ህብረተሰቡ የአካባቢ ጥበቃ ስራን ባህል አድርጎ እንዲተገብረው በተከታታይ እየተሰራ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የምስራቅ ወለጋ ዞን የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ፋንታሁን ታምሩ ናቸው። ''የተፈጥሮ ሀብትን መንከባከብ እና መተካት እንዲቻል የህብረተሰቡን ግንዛቤ የሚያሳድጉ ስራዎች እየተከናወኑ ነው'' ብለዋል።  
አረንጓዴ ልማትንና ፅዳትን ከአገር ልማት ጋር አስተሳስሮ ለማስቀጠል መገናኛ ብዙሃን የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት የበለጠ ማጠናከር ይኖርባቸዋል
Jun 5, 2025 136
አዲስ አበባ፤ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦አረንጓዴ ልማትንና ፅዳትን ከአገር ልማት ጋር አስተሳስሮ በማስቀጠል ሒደት መገናኛ ብዙሀን የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት የበለጠ ማጠናከር እንዳለባቸው የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ገለፁ። የሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄ የማስጀመሪያ ስነ ስርዓት አካል የሆነ የፓናል ውይይት እየተካሔደ ይገኛል። የፓናል ውይይቱ ፅዱ ኢትዮጵያና የአካባቢ ጥበቃን በሚመለከት የመገናኛ ብዙሃን ሚና በሚል የተዘጋጀ ነው።   ውይይቱን አስመልክቶ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማኅበራዊ ጉዳዮች አማካሪ ሚኒስትር ሙአዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ባስተላለፉት መልዕክት እንደገለፁት፥ ኢትዮጵያውያን አካባቢን ጠብቆ የማቆየት ጥሩ ልምድና ባህል አላቸው። መንግስት በአረንጓዴ ልማትና በአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ በርካታ ስራዎችን ማከናወኑን አስታውቀዋል። ፅዱ ኢትዮጵያ የዚሁ አካል መሆኑን ገልፀው፤ ንቅናቄው የታለመለትን ግብ እንዲመታ መገናኛ ብዙሃን የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት አጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸውም ገልጸዋል። በአገሪቱ የሚከናወኑ የልማት ስራዎች የአካባቢ ጥበቃንና አረንጓዴ ልማትን ታሳቢ አድርገው እየተካሄዱ መሆናቸውንም አንስተዋል። በተለይም መገናኛ ብዙሃን ኢትዮጵያን ፅዱና አረንጓዴ በማድረግ ሒደት ውስጥ ኃላፊነታቸውን ይበልጥ አጠናክረው መወጣት ይገባቸዋል ብለዋል። ለዚህም ሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ አስቻይ ሁኔታን እንደሚፈጥር ጠቁመው፤ በተለይ የማህበረሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ ላይ ተከታታይ የሆኑ ስራዎችን መስራት እንደሚገባ ነው ያሳሰቡት። መገናኛ ብዙሃን በጉዳዩ ላይ ከሚሰሩት ስራ በዘለለ ተምሳሌታዊ ተግባራትን በማከናወን የአረንጓዴ ልማትና የአካባቢ ጥበቃ ስራ አካል መሆን እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። በፓናል ውይይቱ ላይ የህዝብና የንግድ መገናኛ ብዙሃን ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ጨምሮ ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። በፓናል ውይይቱ ላይ የመወያያ ጽሁፍ ያቀረቡ የስራ ሃላፊዎች በበኩላቸው ጽዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ መገናኛ ብዙሃን በአገር ግንባታ ላይ ለሚያከናውኑት ተግባር አጋዠ ነው ብለዋል። የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ በዚሁ ግዜ እንደተናገሩት ባለፉት የለውጥ አመታት መንግስት ዘርፈ ብዙ የልማት ስትራቴጂዎችን በመንደፍ ተግባራዊ አድርጓል።   በሁሉም መስክ እየተመዘገቡ ያሉ ውጤቶችን ለማስቀጠል ዘመናዊና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሆነ የአካባቢ ጥበቃ ስረዓት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት፣ በአካባቢ ጥበቃና መሰል ስራዎች እያከናወነች ያለው ተግባር የላቀ መሆኑን ጠቁመው ይሄንን አጠናክሮ ማስቀጠልና ተደራሽነቱን ማስፋት ይገባል ነው ያሉት። የአረንጓዴ አሻራና የአከባቢ ጥበቃ ጉዳይ የትውልድ ህልውና ጉዳይ መሆኑንገልጸው በዚህ ረገድ መገናኛ ብዙሃን ሃላፊነታቸውን በተቀናጀ መልኩ ሊወጡ ይገባል ብለዋል።   የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሳምሶን መኮንን (ዶ/ር) በበኩላቸው መገናኛ ብዙሃን በአገራዊ ጉዳዮችና በዜጎች ተጠቃሚነት ዙሪያ የጋራ አቋም ኖሯቸው በትብብር መስራት እንደሚጠበቅባቸው ነው ያብራሩት ። ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የዜጎችን ተሳትፎና ርብርብ የሚጠይቅ በመሆኑ የንቅናቄውን ዓላማ እንዲሳካ መገናኛ ብዙሃኑ የሚያደርጉት ጥረት ለአገር ሁለንተናዊ እድገት ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል።   የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አድማሱ ዳምጠው፤ ፅዱ ኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን በህዝቦች አንድነትና ትስስር ዙሪያ ለሚያከናውኑት ተግባር ጉልህ አሰተዋጽኦ ያበረክታል ነው ያሉት። በመሆኑም ንቅናቄው ይዞ የመጣውን እድል በአግባቡ በመጠቀም ለአገር ግንባታ ስራው አሻራ ማኖር ይገባል ብለዋል። የኤን.ቢ.ሲ ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ብሩክ ከበደ እንዳሉት መገናኛ ብዙሃን አገራዊ ጉዳይን ማስቀጠልና ከዳር ማድረስ ይጠበቅባቸዋል።   ፅዱ ኢትዮጵያ የአንደ ተቋም ብቻ ሳይሆን የሁሉም ተቋማትና ዜጎች የጋራ ጉዳይ መሆኑን ማስገንዘብና ማስረዳት ከመገናኛ ብዙሃኑ እንደሚጠበቅም አንስተዋል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ በሰጡት ማጠቃለያ በአካባቢ ጥበቃ፣ በአረንጓዴ አሻራና ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ መገናኛ ብዙሃን ባከናወኑት ተግባር አበረታች ውጤት ማምጣት ተችሏል።   የአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ የዜጎችን ግንዛቤ ማደግን የሚጠይቅ በመሆኑ መገናኛ ብዙሃን በዚህ ረገድ የሚያከናውኑት ተግባር ጉልህ ፋይዳ አለው ነው ያሉት። በመሆኑም በሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ መገናኛ ብዙሃን የሚያከናውኑትን ተግባር ይበልጥ በማጠናከር ከብክለት የጸዳች ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሒደት ትብብራቸውን እንዲያጠናክሩም መልእክት አስተላልፈዋል።        
የአካባቢ ብክለትን መከላከልና የአረንጓዴ ልማት ስራን ወጥነት ባለው መልኩ በማከናወን ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ማድረግ ይገባል
Jun 5, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦ በመላው ሀገሪቱ የአካባቢ ብክለትን መከላከልና የአረንጓዴ ልማት ስራን ወጥነት ባለው መልኩ በማከናወን ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ማድረግ እንደሚገባ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ ተናገሩ። ሁለተኛው ዙር ሀገር አቀፍ ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በአዲስ አበባ በይፋ ተጀምሯል። በመርሀ ግብሩ መልዕክት ያስተላለፉት የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ የአካባቢ ጥበቃ ጉዳይ የሁሉም ዜጋ ሃላፊነት ነው ብለዋል። ለዚህም የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ጠቁመው፤ ንቅናቄው ህዝቡ በባለቤትነት የሚሳተፍበትን እድል ያመቻቸ መሆኑንም ተናግረዋል።   የመጀመሪያው ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከብክለት የፀዳች ኢትዮጵያን ከመፍጠር በዘለለ ዜጎች በምቹ የኑሮ ሁኔታ የመኖር መብታቸውን ጭምር ያረጋገጠ ነው ብለዋል። በዚህ ረገድ ቀደም ሲል በፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል። ከዛሬ ጀምሮ በሚከናወነው ሁለተኛው ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ወጥነት ያለው የአረንጓዴ ልማትና የአካባቢ ጥበቃ ስራን ማከናወን ይጠበቃል ነው ያሉት። ለስድስት ወራት በሚቆየው በዚሁ ንቅናቄ ከ15 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ዜጎች የገጽ ለገጽ የፅዳት ዘመቻና መሰል ተግባራትን እንዲያከናውኑ ይሰራል ብለዋል። በተለይም ለአካባቢ ጥበቃና ብክለትን ለመከላከል አጋዥ እንዲሆኑ ታልመው የወጡ ህጎች ተግባራዊ እንዲሆኑ ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ በትኩረት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። በአካባቢ ጥበቃና በብክለት ዙሪያ ለማህበረሰቡ ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ በንቅናቄው ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል ተጠቃሽ ነው።
ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ እያስመዘገበች ያለውን ስኬት አጠናክሮ ለማስቀጠል ለአካባቢ ጥበቃ ተግባር ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 5, 2025 96
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ እያስመዘገበች ያለውን ስኬት አጠናክሮ ለማስቀጠል ለአካባቢ ጥበቃ ተግባር ትኩረት እንደተሰጠ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ እና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ ገለፁ። ሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄ ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ እና የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ በማስጀመሪያ መርሀ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት ፅዱ ኢትዮጵያ ለከተሞች እድገትና ለዜጎች ምቹ አካባቢን በመፍጠር ረገድ የማይተካ ሚና አበርክቷል።   ኢትዮጵያ በሁሉም ዘርፍ እያስመዘገበች ያለውን ስኬት ለማስቀጠል የአካባቢ ጥበቃ ተግባር ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት መንግስት ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎችን በማከናወን የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ማሳደግ መቻሉን ተናግረዋል። ከዚህ ጎን ለጎን በፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በተከናወኑ ተግባራት ንፅህና ባህል እንዲሆንና ዘመናዊ የአካባቢ ጥበቃ ስረዓት እንዲዳብር ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል። ይህም የአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነትን ለመቀነስና የጋራ ብልፅግናን ለማረጋገጥ እድል ፈጥሯል ብለዋል። በዚህ ረገድ ፅዱ ኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄን በማካሔድ ለትውልድ የሚተላለፍ የልማት ስራዎችን ማሳካት መቻሉንም ገልጸዋል። በመሆኑም ሁለተኛው ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከዛሬ ጀምሮ ለስድስት ወራት የሚቆይ ሲሆን በመላ ሀገሪቱ ተግባራዊ የሚደረግ ይሆናል።   በመጀመሪያው ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የኮሪደርና የወንዝ ዳር ልማት እንዲሁም የፍሳሽ ማስወገጃ ፕሮጀክቶች፣ የአረንጓዴ ልማት ስራዎች ጨምሮ የመፀዳጃ ቤት ግንባታዎች ተከናውነዋል። ይህም ንቅናቄው ግቡን እንዲመታ ጉልህ አስተዋጽኦ አበርክቷል ብለዋል። በሁለተኛው ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄም የሚከናወኑ ተግባራትን ትኩረት ሰጥቶ ማሳካት እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል። ከብክለት የፀዳች እና ምቹ ከባቢያዊ ሁኔታ ያሟላች ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሂደት ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባም አቶ አደም ፋራህ መልዕክት አስተላልፈዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በበኩላቸው ፅዱ ኢትዮጵያ ሀገራዊ ንቅናቄ በአዲስ አበባ ለሚከናወኑ የልማት ስራዎች ትልቅ መነቃቃትን ፈጥሯል ብለዋል። በከተማዋ የፅዱ ኢትዮጵያ አላማን ከግብ ለማድረስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል። በከተማዋ በተለይም በኮሪደር ልማት ከተማዋን የሚመጥን፣ የዜጎችን ኑሮ የሚያሻሽልና አለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚጨምር የልማት ስራዎች መከናወናቸውንም ገልጸዋል። በተጨማሪም የውሀ ብክለትን መከላካል፣ የፅዳት ዘመቻና የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ስራዎችን ወጥነት ባለው መልኩ ማከናወን መቻሉን ጠቅሰው፤ በዚህም ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት መቻሉን ከንቲባዋ አንስተዋል። ለአብነትም በከተማዋ ያሉ ወንዞችን ከብክለት በመከላከልና በመጠበቅ ረገድ ስር ነቀል ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በ44 ወንዞች ላይ የወንዝ ዳርቻ የልማት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው፤ ወንዞች የብክለት መንስኤ ሳይሆኑ የቱሪስት መስህብ እንዲሆኑ የማድረግ ስራ ትኩረት ተሰጥቶታል ነው ያሉት። በተጨማሪም የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ አካል የሆኑ መፀዳጃ ቤቶች ግንባታ፣ የዘመናዊ የፍሳሽ ማስወገጃ ጣቢያዎች፣ የህዝብ መዝናኛ ፓርኮችና የህፃናት መዝናኛና መጫወቻ ስፍራዎችን በአጭር ጊዜ ገንብቶ በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት ማድረግ ተችሏል ብለዋል። እነዚህንና መሠል ስራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር ሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ አስቻይ ሁኔታን እንደሚፈጥር ጠቁመዋል። በቀጣይም ከተማዋን የሚመጥኑና የነዋሪዎችን ኑሮ የሚያሻሽሉ የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
በድሬዳዋ የጎርፍ አደጋን ቀድሞ መከላከል የሚያስችሉ ሥራዎች ተከናውነዋል - ባለስልጣኑ
Jun 5, 2025 66
ድሬደዋ፤ ግንቦት 28/2017(ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ አስተዳደር ከግማሽ ቢሊዮን ብር በላይ ወጪ የተለያዩ የጎርፍ መከላከያ ሥራዎች መከናወናቸውን የአስተዳደሩ መንገዶች ባለስልጣን አስታወቀ። የአየር ንብረት ለውጥን ተከትሎ በሚከሰት የጎርፍ አደጋ ለችግር ከሚጋለጡ የሀገራችን ክፍሎች ድሬዳዋ አንዷ ናት። የአስተዳደሩ የአካባቢ፣ የደንና አየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን እንደገለጸው፣ ባለፉት ዓመታት በድሬዳዋ በአረንጓዴ አሻራ እና በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ የተከናወኑ ሥራዎች የጎርፍ አደጋ ስጋትን አስቀርቷል። በተለይም በሐምሌ ወር 1998 ዓ.ም ከተጎራባች የምስራቅ ሐረርጌ ወረዳዎች በመምጣት ድሬዳዋን ያወደመው የጎርፍ አደጋ እንደሀገር ወደር አይገኝለትም ብለዋል። የአስተዳደሩ የመንገዶች ባለስልጣን የመንገድ ግንባታ ጥገናና አስተዳደር ዳይሬክተር ያሲን መሐመድ ለኢዜአ እንዳስታወቁት፤ ከ1998ቱ ክስተት በኋላ የተቀናጀ የጎርፍ መከላከል ስራዎች ተሰርተዋል። በጎርፍ መነሻ እና መከሰቻ ወንዞችና አካባቢዎች ላይ የጎርፍ መከላከያ ግንቦች ተገንብተው አደጋውን መቀነስ ተችሏል ብለዋል። ዘንድሮ እና አምና በደቻቱና በጎሮ ወንዞች ላይ ከ548 ሚሊዮን ብር በላይ በጀት ወጪ ወንዙ የተፈጥሮ ፍሰቱን ጠብቆ እንዲጓዝ ያስቻሉ የተለያዩ ልማቶች ተከናውነዋል ብለዋል። እንደ ዳይሬክተሩ ገለጻ በአስተዳደሩ ገጠር ቀበሌዎች የሚከሰትን የጎርፍ አደጋ በመከላከል በኩል ውሃውን ለልማት ማዋል ያስቻሉ ሥራዎች ተከናውነዋል። በተለይም ከሁለት ዓመት በፊት በጎርፍ የፈረሰውን ድልድይ በዘመናዊ መንገድ በ137 ሚሊዮን ብር ወጪ መገንባቱ የጎርፍ ስጋትን አስቀርቷል ብለዋል። በድሬዳዋ አስተዳደር የአካባቢ፣ ደንና አየር ንብረት ባለስልጣን የደን ልማት ዳይሬክተር ማስረሻ ይመር በበኩላቸው ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ፣ በተፋሰስ ልማትና በተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ የተከናወኑ ሥራዎች የጎርፍ አደጋን ማስቀረት ችለዋል ነው ያሉት። በተጨማሪም ከተለያዩ አካላት ጋር በመቀናጀት የጎርፍ ምንጭ በሆኑ ተፋሰሶች ላይ እየተሰሩ ያሉ ተግባራት ተጨባጭ ለውጦች ማምጣታቸውን አስረድተዋል። ዘንድሮም ለጎርፍ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ማህበረሰቡን የማንቃት ሥራ እየተሰራ መሆኑን የገለፀው ደግሞ የድሬዳዋ አስተዳደር አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ነው። በኮሚሽኑ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ምላሽ ቡድን መሪ ወንድወሰን በሪ እንዳሉት፤ አደጋን አስቀድሞ ከመከላከል ባሻገር ድንገት ለሚፈጠር ችግር ምላሽ መስጠት የሚያስችል ዝግጅት ተደርጓል።
የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎች ብክለትን በመከላከል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ መስጠት በሚያስችል መልኩ እየተገነቡ ነው
Jun 4, 2025 100
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 27/2017(ኢዜአ)፦ የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎች ብክለትን በመከላከል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ መስጠት በሚያስችል ሁኔታ እየተገነቡ መሆኑን የኢፌዴሪ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ ገለጹ። ነገ ግንቦት 28/2017 ዓ.ም በኢትዮጵያ ለ32ኛ በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ52ኛ ጊዜ የሚከበረውን የዓለም የአካባቢ ቀን ተከትሎ 2ኛው ዙር ሀገር አቀፍ የጽዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ይካሄዳል።   ለስድስት ወራት በሚቆየው 2ኛው ዙር ሀገር አቀፍ የጽዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄም ግንዛቤ ማስጨበጫ ስራን ጨምሮ በሕግ ተከባሪነት ውጤት ላስመዘገቡ ተቋማትና ግለሰቦች እውቅና እንደሚሰጥ ተገልጿል። ቀኑን አስምልክቶም የፌደራል፣ የክልልና የከተማ አስተዳደር የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የስራ ኃላፊዎች የአዲስ አባባ የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶችን የስራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል።   በዚሁ ወቅት የኢፌዴሪ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ሌሊሴ ነሜ(ኢ/ር)፤ በአዲስ አበባ በወንዝ ዳርቻ ልማት እየተገነቡ የሚገኙ ፕሮጀክቶች መዲናዋን ጽዱ በማድረግ ውብ ገጽታ እያላበሷት ነው ብለዋል። በጉብኝቱም በእንጦጦ ፓርክ የወንዝ ዳርቻ ፕሮጀክት የሚሳተፉ የኮንሶ የአፈር እቀባና እርከን ስራ ሙያተኞች ሀገር በቀል ዕውቀትን የገለጠ ስኬታማ ስራ እየሰሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ከእንጦጦ ተራራ ጀምሮ የሚገነባው የወንዝ ዳርቻ የአፈር እቀባና የእርከን ስራ ፕሮጀክት የጎርፍ አደጋ ተጋላጭነትን በመቀነስ በታችኛው ተፋሰስ ላይ ምቹ የግብርና ልማት ዕድል እንደሚፈጥርም ተናግረዋል። አዲስ አበባን ጨምሮ በክልል ከተሞች እየተከናወኑ የሚገኙ የኮሪደር ልማት ስራዎች የአካባቢ ደኅንነትን በመጠበቅ ለዜጎች ምቹ የኑሮ ምኅዳር እየፈጠረላቸው እንደሚገኝ አንስተዋል። የከተሞች የኮሪደርና የአረንጓዴ አሻራ ልማት ስራዎችም የአካባቢን ጽዳትና ውብት በማጎናጸፍ ለአካባቢ ጥበቃ ስራ አዎንታዊ ሚና እየተወጡ መሆኑን አስረድተዋል። የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶችም ብክለትን በመከላከል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ መስጠት በሚያስችል መልኩ እየተገነቡ እንደሚገኙ አብራርተዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ ዲዳ ድሪባ፤ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ጉልህ ፋይዳ እያበረከቱ ነው ብለዋል። የወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎች አፈርና ውሃን በመጠበቅ የመዲናዋን ነዋሪዎች የጎርፍ አደጋ ተጋላጭነት እየቀረፉ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በቀጣይም የመዲናዋን ወንዞች ከብክለት በመጠበቅ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው አገልግሎቶች እንዲሰጡ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የደን፣ አካባቢ ጥበቃና ልማት ቢሮ ኃላፊ ግዛተ ጊጄ፤ የአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች የአካባቢ ደህንነትን በመጠበቅ ትምህርት የሚወሰድባቸው ናቸው ብለዋል።   የጋምቤላ ክልል የአካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ቢሮ ኃላፊ ቻንግ ዑቦንግ፤ የመዲናዋ የወንዝ ዳርቻ ልማት ሀገር በቀል ዕፅዋቶችን የሚጠብቅ አስደናቂ ስራዎች መሆናቸውን እንደተገነዘቡ ገልጸዋል።
በመዲናዋ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ እውን የሚያደርጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Jun 4, 2025 95
አዲስ አበባ፤ግንቦት 27/2017(ኢዜአ)፦በመዲናዋ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ እውን የሚያደርጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙ የአዲስ አበባ ከተማ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ዲዳ ድሪባ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ባለስልጣኑ በከተማው የአካባቢ፣የአየርና የወንዞችን ብክለት መከላከል የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በከተማ ደረጃ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ እውን የሚያደርጉ ውጤታማ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡ ለአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ የማይበገር ከባቢን ለመፍጠርም የስነ-ህይወታዊና የስነ-አካላዊ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙም ተናግረዋል፡፡ በከተማዋ ለአረንጓዴ ልማት የተለዩ አካባቢዎች ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ እየተደረጉ ያሉ ስራዎችም ውጤታማ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ የሙቀት አማቂ ጋዝ ልቀትን መቀነስ የሚያስችሉ አማራጭ ኢነርጂዎች እንዲስፋፉ ቢሮው በርካታ ስራዎችን እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ የወንዞች ብክለትን በመከላከል ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎት እንዲሰጡ ለማስቻልም የወንዝ ዳርቻ ልማት በስፋት እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ከእንጦጦ ተራራ እስከ ፒኮክ 42 ኪሎ-ሜትር ስፍራዎች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡ ይህም የወንዞችና የአካባቢ ብክለትን ከመከላከል ባለፈ ዜጎች በፅዱና ምቹ አካባቢ እንዲኖሩ የማስቻል ተግባር ነው ብለዋል። በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎች መበራከታቸው ብሎም ህብረተሰቡ ለአረንጓዴ አሻራ የሰጠው ትኩረት በከተማዋ ብክለትን ለመቀነስ ትልቅ ድርሻ እየተወጣ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የአማሔ የኤሌክትሪክ ዕቃዎች ማምረቻ ማህበር መስራችና ስራ አስኪያጅ አቶ ዮሐንስ አየለ፥ ማህበራቸው የአየር ብክለትንና የደን መጨፍጨፍን የሚያስቀሩ ኃይል ቆጣቢ ምድጃዎችና ምጣዶች በማምረት ላይ መሆኑን ተናግረዋል። የየካ ክፍለ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ታየች ወልደስንበት እና የለሚ ኩራ ከፍለ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ መሳይ ተክሌ በቤታቸው ማገዶ ቆጣቢ ምድጃና ምጣድ እየተጠቀሙ መሆናቸውን ገልጸዋል። ይህም ኢትዮጵያ የጀመረችው አረንጓዴ ኢኮኖሚ እውን የሚያደርግና ጊዜ ቆጣቢ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ለዜጎች ኑሮ ምቹ የሆኑና ከብክለት የጸዱ አካባቢዎችን እየፈጠረ ነው
Jun 3, 2025 104
አዲስ አበባ፤ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ለዜጎች ኑሮ ምቹ የሆኑና ከብክለት የጸዱ አካባቢዎችን እየፈጠረ እንደሚገኝ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ ገለጹ። ከግንቦት 28 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በአገር አቀፍ ደረጃ የሚካሔደውን ሁለተኛ ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ አስመልክቶ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ ለጋዜጠኞች መግለጫ ሰጥተዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ52ኛ ጊዜ በሀገር ዓቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ32ኛ ጊዜ የሚከበረው የዓለም የአካባቢ ቀን ግንቦት 28 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ በተለያዩ ኹነቶች እንደሚከበር አስታውቀዋል። በዕለቱ ሁለተኛው ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በይፋ እንደሚጀመርም ዋና ዳይሬክተሯ በመግለጫቸው አንስተዋል። ዋና ዳይሬክተሯ የመጀመሪያው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ውጤታማ ተግባራት የተከናወኑበት እንደነበር አስታውሰዋል። የመጀመሪያው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከብክለት የፀዳች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አስቻይ ሁኔታን መፍጠሩንም አንስተዋል። ሁለተኛው ዙር ንቅናቄው በአገር አቀፍ ደረጃ ለስድስት ወራት እንደሚካሄድ ገልጸው፤ በአንደኛው ዙር የተጀመሩ ተግባራትን ይበልጥ አጠናክሮ ለማስቀጠል ያግዛል ብለዋል። በንቅናቄው የውሀ ብክለትን መከላከል፣የፅዳት ዘመቻና የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ስራዎች ወጥ በሆነ መልኩ እንደሚተገበሩ አስታውቀዋል። የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ለዜጎች ኑሮ ምቹ የሆነና ከብክለት የጸዳ አካባቢያዊ ሥነ-ምህዳር እየተፈጠረ ለመምጣቱ ማሳያ ነው ብለዋል። ለስድስት ወራት በሚቆየው አገር አቀፍ ንቅናቄ ከ15 ሚሊዮን በላይ ዜጎች በጉዳዩ ላይ የተለያዩ ተግባራትን የሚያከናውኑበት ሁኔታ እንደሚፈጠርም ጠቁመዋል። የመጀመሪያው ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ እንደ አገር በአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ ያሉ ክፍተቶችን ለማረምና የማህበረሰቡን ግንዛቤ ለማዳበር ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም አክለዋል። ለአብነትም በአካባቢ ጥበቃ ዙሪያ አዋጆችና ህጎች እንዲሻሻሉ ምቹ ሁኔታ የተፈጠረበት መሆኑን ጠቁመው፤ በአሁኑ ወቅት የአካባቢ ጥበቃና ደህንነት ጉዳይ እየዳበረና ባህል እየሆነ መጥቷል ብለዋል። ንቅናቄው “ፅዱ ኢትዮጵያ እስከ ባሕል” በሚል መሪ ሃሳብ እንደሚካሄድ ተገልጿል።
የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስ ፤የዜጎች ደህንነትና ጤንነትን ለማስጠበቅ ምቹ ምህዳር የሚፈጥር ነው -ቋሚ ኮሚቴው
Jun 3, 2025 123
አዲስ አበባ፤ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስ ፤የዜጎች ደህንነትና ጤንነትን ለማስጠበቅ ምቹ ምህዳር የሚፈጥር መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፤መስኖ፣ቆላማ አካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 33ኛ መደበኛ ስብሰባውን ዛሬ አካሂዷል። ምክር ቤቱ በስብሰባው የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ረቂቅ አዋጅ ላይ የተወያየ ሲሆን አዋጁን መርምሮ አጽድቋል።   በምክር ቤቱ የውሃ ፤ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና አካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር) አዋጁን አስመልክቶ ሪፖርትና የውሳኔ ሀሳብ አቅርበዋል። በዚህም አዋጁ በቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ላይ የሕግ ጥሰቶች ካሉ የእርምት እርምጃዎችን መውሰድ የሚያስችሉ ድንጋጌዎች የተካተቱበት ነው ብለዋል። ከመኖሪያ ቤት 20 ሜትር ርቀት ድረስ ማጽዳት ግዴታ መሆኑ በአዋጁ መደንገጉን ጠቁመዋል፡፡ ለአካባቢ ብክለት የሚዳርጉ እና አንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ ምርቶች በሥነ ምህዳር ላይ የሚያደርሱትን ጉዳት መከላከል ሌላው የአዋጁ ዓላማ መሆኑን አብራርተዋል። የቆሻሻ አወጋገድን ዘመናዊ እና ሳይንሳዊ ማድረግ አዋጁ ከያዛቸው ጉዳዮች መካከል መሆኑን የጠቆሙት ምክትል ሰብሳቢው የሚወገደው ቆሻሻ መልሶ ጥቅም ላይ እንዲውል ማስቻልንም ያካተተ ነው ብለዋል። አዋጁ በሁሉም ክልሎች ተፈጻሚ እንደሚሆን አስታውቀው በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ዘላቂነት ያለው የቆሻሻ አያያዝ ሥርዓት ለመዘርጋት አዋጁ መሰረት የሚጥል መሆኑንም አብራርተዋል። አዋጁ በሰዎች ደህንነት እና በአካባቢ ደህንነት ላይ እየደረሰ ያለውን ጉዳት በተሻለ መልኩ ለመከላከል ዕድል ይፈጥራል ነው ያሉት። የምክር ቤቱ አባላት በበኩላቸው አዋጁ የዜጎችን ጤናና ደህንነት ለማስጠበቅ ፋይዳው ጉልህ መሆኑን አንስተዋል። በተለይም በአዋጁ ዙሪያ የህብረተሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ እንደሚገባ ጠቁመው አዋጁ ውጤታማ በሆነ መልኩ እንዲተገበር የባለድርሻ አካላትን የተቀናጀ ትብብር እንደሚጠይቅም አጽንኦት ሰጥተዋል። ምክር ቤቱ በደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ የተወያየ ሲሆን አዋጁን አዋጅ ቁጥር 1383/2017 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል።          
ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከብክለት የፀዳች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አስቻይ ሁኔታን ፈጥሯል
Jun 3, 2025 118
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 26/2017(ኢዜአ)፦ የመጀመሪያው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከብክለት የፀዳች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አስቻይ ሁኔታ መፍጠሩን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ ገለጹ። ሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግንቦት 28/2017 ዓ.ም ጀምሮ በሀገር አቀፍ ደረጃ እንደሚካሄድ ተገልጿል። ንቅናቄውን አስመልክቶ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ዳይሬክተሯ በዚህ ወቅት እንደገለጹት፤ የመጀመሪያው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ውጤታማ በሆነ መልኩ ተካሂዷል። የመጀመሪያው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከብክለት የፀዳች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ አስቻይ ሁኔታን መፍጠሩን አንስተዋል። ሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግንቦት 28/2017 ዓ.ም ጀምሮ ለስድስት ወራት በሀገር አቀፍ ደረጃ እንደሚካሄድ ገልጸው፤ በአንደኛው ዙር የተጀመሩ ተግባራትን ይበልጥ አጠናክሮ ለማስቀጠል ያግዛል ብለዋል። በንቅናቄው የውሀ ብክለትን መከላከል፣ የፅዳት ዘመቻና የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ስራዎች ወጥ በሆነ መልኩ እንደሚተገበርም አስታውቀዋል።
በከተማው የሚጣሉ የፕላስቲክ ቆሻሻዎችን በአግባቡ በመሰብሰብ ጥቅም እንዲውሉ እየተደረገ ነው
Jun 2, 2025 117
ደብረ ማርቆስ፤ ግንቦት 25/2017(ኢዜአ)፡- በደብረማርቆስ ከተማ የሚጣሉ የፕላስቲክ ቆሻሻዎችን በአግባቡ በመሰብሰብ ለመልሶ ጥቅም እንዲውሉ እየተደረገ መሆኑ ተመለከተ። በየቦታው ያለአግባብ በሚጣሉ የፕላስቲክ ቆሻሻዎች ምክንያት ሊከሰት የሚችለውን የአካባቢ ብክለት ለመከላከል የድርሻቸውን እየተወጡ እንደሚገኙ የከተማው ነዋሪዎች ገልጸዋል። የከተማ አስተዳደሩ "የፕላስቲክ ብክለትን እንግታ" በሚል ሃሳብ የአለም የአካባቢ ቀንን ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ ዛሬ የውይይት መድረክ ያካሄደ ሲሆን፤ ከውይይቱ ተሳታፊ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ሰርካለም አዝመራው፤ አካባቢን የሚበክሉ ቆሻሻን በአግባቡ ተሰብስቦ እንዲወገድ የበኩላቸውን እየተወጡ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይ በአካባቢያቸው የሚጣሉ የፕላስቲክ ቆሻሻዎችን ሰብስበው ጥቅም ላይ እንዲውሉ ለሚያደርጉ የተደራጁ ማሀበራት እየሰጡ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል። ሌላው የውይይቱ ተሳታፊ ወጣት ይትባረክ ውዱ በበኩሉ፤ አካባቢን የሚበክሉ ቁሳቁሶችን በመሰብሰብ አካባቢያቸውን ጽዱና ውብ ከማድረግ በተጨማሪ የገቢ ምንጭም እያገኘበት መሆኑን ገልጿል።   በየቦታው ያለአግባብ በሚጣሉ የፕላስቲክና ሌሎች ቆሻሻዎች አካባቢን እንዳይበክሉ አስተዳደሩ በሚያደርገው እንቅስቃሴ ላይ በመሳተፍ ድጋፉን እንደሚያጠናክር ተናግሯል። የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ስለሺ ተመስገን፤ በአካባቢያችን የሚጣለው የፕላስቲክ ቆሻሻ በሰውና እንስሳት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያስከትላል ብለዋል። በመሆኑም የአካባቢ ቆሻሻን በአግባቡ በመሰብሰብ ለመልሶ ጥቅም እንዲውል በማድረግ አካባቢን ከብክለት ለመከላከል በከተማ አስተዳደሩ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የዛሬው ውይይት ዓላማም የፕላስቲክ ቆሻሻ ለአካባቢ ብክለት ያለውን ተፅዕኖ ለማህበረሰቡ ግንዛቤ በማስጨበጥ ቆሻሻን ሲያከማቹ በዘርፍ በዘርፍ ለይተው እንዲያከማቹ የሚያግዝ ነው ብለዋል። የከተማ አስተዳደሩ አካባቢ ጥበቃ ፅዳትና ውበት አረንጓዴ ልማት ተጠሪ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ቸርነት አለማየሁ በበኩላቸው እንዳሉት፤ የፕላስቲክ ቆሻሻ በአፈር፣ በውሃ፣ በአካባቢ ስነውበትና በአየር ላይ ብክለት የሚያስከትል ነው። ችግሩን ለመግታት በደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ላይ የሚሰሩ ማህበራትን በማጠናከር መልሶ ጥቅም ላይ እንዲውል እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።
በከተማ አስተዳደሩ ለክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የችግኝ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Jun 2, 2025 133
ጅማ፣ግንቦት 25/2017(ኢዜአ):- በጅማ ከተማ አስተዳደር ለክረምቱ ወቅት የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያላቸው ችግኞች ተዘጋጅተዋል። በጅማ ከተማ የከተማ ግብርና ጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት አስተዳደር ቡድን መሪ አቶ መሀመድ ሀሰን እንዳሉት ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ለዛፍና ለምግብነት የሚውሉ ችግኞች ተዘጋጅተዋል። ባለፉት ዓመታት በመርሃ ግብሩ የተተከሉት ችግኞች የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመቀየርና የከተማን ውበት ከመጨመር አንጻር ለመጪው የተከላ መርሃ ግብር መነሳሳትን ፈጥሯል ብለዋል።   በዚህ ክረምት ለተከላ ከተዘጋጁ ችግኞች ውስጥ የሻይ ቅጠል፣ ለከተማ ውበት የሚሆኑ፣ ፍራፍሬዎች እና ለእንስሳት መኖ የሚሆኑ ናቸው ብለዋል። አቶ መሀመድ አክለውም በችግኝ ዝግጅቱ ለምግብነት የሚውሉ በአትክልት እና ፍራፍሬ ልማት ሙዝ፣ ፓፓያ፣ አቮካዶ፣ ማንጎ እና የመሳሰሉ ይገኙበታል ብለዋል። የችግኝ ዝግጅቱ በአምስት ቀበሌዎች ባሉ የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች የተካሄደ ሲሆን ለችግኞቹም እንክብካቤ እየተደረገላቸው መሆኑን ተናግረዋል።   በጅሬን ቀበሌ ችግኝ ጣቢያው ችግኝ በመንከባከብ ላይ የተሰማሩት ሮዛ ሀሰን እንዳሉት በክረምት ወቅት የሚተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ ከሚያገኙት ወርሃዊ ገቢ ባለፈ ለአረንጓዴ አሻራው መርሃ ግብር የበኩላቸውን እያበረከቱ መሆናቸውን ገልጸዋል። የጅሬን ቀበሌ አርሶ አደር አቶ ኢብራሂም አብደላ በበኩላቸው በክረምት ወቅት የሚተከሉ ችግኞችን በግላቸው ማፍላታቸውን ተናግረዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም