አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ልማት ስራዋን በኮፕ28 ጉባኤ ላይ እያስተዋወቀች ትገኛለች
Nov 30, 2023 70
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ልማት ስራዋን በኮፕ28 ጉባኤ ላይ ባለው የኢትዮጵያ አውደ ርእይ/ፓቪሊዮን/ በማስተዋወቅ ላይ ትገኛለች። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ እና ግርማዊ ሼህ ሞሀመድ ቢን ዛይድ አል ናሕያን ከዐውደ ርዕዩ ይፋዊ መክፈቻ አስቀድሞ የኢትዮጵያን ፓቪሊዮን መጎብኘታቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት አስታውቋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሼህ ሞሀመድ ቢን ዛይድ አል ናህያንን ኢትዮጵያ ለአየር ጠባይ ለውጥ መከላከል እየከወነች ያለችውን ተጨባጭ መፍትኄ ለማሳየት የቀረበችበትን የኢትዮዽያን የአረንጓዴ አሻራ መካነ ርዕይ/ፓቪሊዮን/ ስለጎበኙ አመሰገኑ
Nov 30, 2023 59
አዲስ አበባ፤ ህዳር 20/2016 (ኢዜአ) ፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሼህ ሞሀመድ ቢን ዛይድ አል ናህያንን ኢትዮጵያ ለአየር ጠባይ ለውጥ መከላከል እየከወነች ያለችውን ተጨባጭ መፍትኄ ለማሳየት የቀረበችበትን የኢትዮዽያን የአረንጓዴ አሻራ መካነ ርዕይ/ፓቪሊዮን/ ስለጎበኙ አመሰገኑ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ወንድሜ ሼህ ሞሀመድ ቢን ዛይድ አል ናህያንን ኢትዮጵያ ሀገራችን ለአየር ጠባይ ለውጥ መከላከል እየከወነች ያለችውን ተጨባጭ መፍትኄ ለማሳየት የቀረበችበትን የኢትዮዽያን የአረንጓዴ አሻራ መካነ ርዕይ/ፓቪሊዮን/ ስለጎበኙ አመሰግናለሁ ብለዋል።
አፍሪካ በተ.መ.ድ የአየር ንብረት ጉባዔ /ኮፕ 28/ የጋራ አጀንዳዋን በአንድ ድምፅ ታሰማለች
Nov 28, 2023 76
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 18/2016 (ኢዜአ) ፡- አፍሪካ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባዔ /ኮፕ 28/ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል "አንድ ድምፅ" ታሰማለች ሲል አፍሪካ ኅብረት ገለፀ። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባዔ (ኮፕ 28) በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ፤ በዱባይ ከነገ በስቲያ ይጀመራል። በጉባዔው የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የተደረሱ ስምምነቶችና ድንጋጌዎች ተግባራዊነታቸው ምን ላይ እንደደረሰ ይገመግማል። ጎን ለጎን አገራት የአየር ንብረት ለማቋቋም በተለይም የታዳሽ ኃይል አማራጮችን በማስፋት እየተሰሩ ያሉ ሥራዎች ምክክር ይደረግባቸዋል። ታዳጊ አገራት በአየር ንብረት ለውጥ የሚደርስባቸውን አደጋ ለመቋቋምና የኃይል ሽግግር እንዲያደርጉ የሚያስችሉ የፋይናንስ አቅርቦት ላይም ጉባዔው ትኩረት ያደርጋል ተብሏል። በተጨማሪም የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል አገራት አዲስ የትብብር ማዕቀፍ ሊፈጥሩ እንደሚችሉም ጉባዔው ከወዲሁ ትልቅ ግምት ተሰጥቶታል። ጉባዔውን በማስመልከት ኢዜአ ያነጋገራቸው የአፍሪካ ሕብረት የግሪን ዎል ኢንሼቲቭ ዳይሬክተር ኢልቪስ ፖል፤ አፍሪካ አጀንዳዋን በጉባዔው በአንድ ድምፅ ታሰማለች ብለዋል። ጉባዔው ከዚህ ቀደም በአህጉሪቱ የአየር ንብረት ለውጥ ለመቋቋም የተደረሱ ስምምነቶች ወደ ተግባር ለመቀየርና በዘርፉ የፋይናንስ አቀርቦትን ለማስፋት ዕድል እንደሚፈጥር ገልፀዋል። የአፍሪካ ሕብረት የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የብሉ ኢኮኖሚና የዘላቂ አካባቢ ኮሚሽነር አምባሳደር ጆሴፋ ሳኮ፤ አፍሪካ በጉባዔው በንቃት ትሳተፋለች ብለዋል። በተለይም በቅርቡ በኬንያ ናይሮቢ በተካሄደው የአፍሪካ ሕብረት የአየር ንብረት ጉባዔ በጋራ የተያዙ አቋሞች አፍሪካ በጉባዔው ውጤታማ ተሳትፎ እንዲኖራት መሠረት ይጥላል ብለዋል። ይህንንም ተከትሎ አፍሪካ በጉባዔው የአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ቀዳሚ አጀንዳዋ ታደርጋለች ነው ያሉት። አፍሪካ ምንም እንኳን የበካይ ጋዝ ልቀቷ አነስተኛ ቢሆንም በአየር ንብረት ለውጥ አህጉሪቱ ድርቅ፣ ጎርፍና መሰል የተፈጥሮ አደጋዎች እያስተናገደች ትገኛለች። አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ የደረሰባትን ጉዳት ለመቋቋምና ወደ ታዳሽ ኃይል ሽግግር እንድታደርግ የፋይናንስ ድጋፍ ማፈላለግ ሌላኛው አጀንዳዋ እንደሚሆን አንስተዋል። የዓለም ሙቀት የመጨመር ምጣኔ በአማካይ ከ1 ነጥብ 5 እስከ 2 ዲግሪ ሴሊሽየስ ለማድረግ የተደረሰው የፓሪስ ሥምምነት እውን ለማድረግ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2030 የዓለም የበካይ ጋዝ የልቀት ምጣኔ ከ28 እስከ 40 በመቶ መቀነስ እንዳለበት የተባበሩት መንግሥታት ደርጅት መረጃ ያሳያል። በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ዱባይ ኅዳር 20 የሚጀምረው የመንግሥታቱ ድርጅት የአየር ንብረት ጉባዔ (ኮፕ 28) እስከ ታህሳስ 2 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል።
በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተተከሉ ችግኞች ውስጥ 60 በመቶ በጥምር ግብርና የለሙ ናቸው--ዶክተር ግርማ አመንቴ
Nov 26, 2023 146
ሀዋሳ ፤ህዳር 16/2016 (ኢዜአ)፦ በሁለተኛው ምዕራፍ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከተተከሉ ችግኞች መካከል 60 በመቶ የሚሆኑት በጥምር ግብርና የለሙ መሆናቸውን የግብርና ሚንስትሩ ዶክተር ግርማ አመንቴ ገለጹ። ህብረተሰቡ ለተተከሉ ችግኞች ተገቢውን እንክብካቤ እንዲያደርግም ጥሪ አቅርበዋል። ሚኒስትሩ ባለፈው የክረምት ወቅት በሲዳማ ክልል በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተተከሉ ችግኞች እየተደረገ ያለውን የእንክብካቤ ሥራ ዛሬ በመስክ ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ወቅት ዶክተር ግርማ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በመንግስት አቅጣጫ መሠረት በሁለተኛው ምዕራፍ ከሚተከሉ ችግኞች መካከል 60 በመቶ የሚሆኑት በጥምር ግብርና እንዲለሙ ተደርጓል። በእዚህም ፍራፍሬና የእንስሳት መኖን በጥምር ለማልማት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። ከሚተከሉ ችግኞች 60 በመቶውን በጥምር ግብርና እንዲለማ የተደረገበት ምክንያት የግብርና ምርትና ምርታማነትን በዘላቂነት ለማሳደግ ታስቦ መሆኑንም አስረድተዋል። ቀሪዎቹ የተተከሉ ችግኞች ለደን ልማትና ለከተማ ውበት የሚያገለግሉ መሆናቸውንም ዶክተር ግርማ ገልጸዋል። “በክረምቱ ለተተከሉ ችግኞች በህዝብ ተሳትፎ እየተደረገ ባለ የእንክብካቤ ሥራ የተሻለ የጽድቀት መጠን ላይ ይገኛሉ” ብለዋል። "የጥምር ግብርና በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ የሚሰራና አርሶ አደሩም ጥቅሙን እስካየ ድረስ በየቀኑ የማረም፣ ውሃ የማጠጣትና የመንከባከብ ሥራ ስለሚሰራ የጽድቀት መጠኑ ከፍ ይላል" ብለዋል። በዚህ ረገድ በሲዳማ ክልልም ሆነ እንደአገር የተሰራው ሥራ መልካም መሆኑን ጠቅሰው፤ በበጋ ወራትም የችግኝ እንክብካቤ ሥራው ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል። የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው እንዳሉት፣ በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ የተያዘውን መርሃ ግብር ለማሳካት እየሰራ ነው። በክልሉ ባለፈው ዓመት ብቻ ስነ ምህዳርን መሠረት ባደረገ መልኩ 306 ሚሊዮን የተለያየ ጥቅም የሚሰጡ ችግኞች መተከላቸውን ጠቁመዋል። የጥምር ግብርና ልማትን ለማሳካት ለቡና፣ ፍራፍሬ እና እንስሳት መኖ ልማት ትኩረት መሰጠቱንም አስታውሰዋል። በክልሉ የተተከሉ ችግኞች የጽድቀት መጠን በአማካይ ከ85 በመቶ በላይ መሆኑን ገልጸው፣ ከህብረተሰቡ ጋር በመሆን ለችግኞች የሚደረገው የእንክብካቤ ሥራ ቀጣይ እንደሚሆን አመልክተዋል። በሲዳማ ክልል ሸበዲኖ ወረዳ የሞርቾ ነጋሽ ቀበሌ አርሶ አደር ጦና ጦምራ በሰጡት አስተያየት ስልጠና ወስደው የጥምር ግብርና ሥራ መጀመራቸውን ገልጸዋል። ባላቸው አነስተኛ መሬት ላይ የተሻሻሉ የአቮካዶ ችግኞችን ከቡናና እንሰት ጋር አቀናጅተው ማልማታቸውን ገልጸዋል። ለመጀመሪያ ጊዜ ካለሙት አቦካዶ 25 ኩንታል ለይርጋለም የተቀናጀ የግብርና ምርቶች ማቀነባበሪያ ኢንዱስትሪ በማቅረብ 87 ሺህ ብር ገቢ ማግኘታቸውን ተናግረዋል። በቀጣይ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ 580 የአቮካዶ ችግኞችን በመትከል እየተንከባከቡ መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
የግብርና ሚኒስትሩና የሲዳማ ክልል አመራሮች ችግኞችን ተንከባከቡ
Nov 26, 2023 95
አዲስ አበባ ፤ኅዳር 16/ 2016/ (ኢዜአ)፦ የግብርና ሚኒስትሩና የሲዳማ ክልል ከፍተኛ አመራሮች በአዋሳ የታቦር ተራራ ላይ የተተከሉ ችግኞችን ተንከባከቡ ፡፡ የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት ለአረንጓዴ አሻራ የተጣለውን ግብ ለማሳካት በክረምት ወቅት የተተከሉ ችግኞችን ጽድቀት በቅርበት መከታተልና መንከባከብ ይገባል ። ማህበረሰቡም ሆነ ተቋማት በክረምት ወቅት የተከሏቸውን ችግኞች የመንከባከብና ውሃ የማጠጣት ስራ አጠናክረው መቀጠል ይኖርበቸዋል ነው ያሉት ። ሚኒስትሩ በሲዳማ ክልል በሚኖራቸው ቆይታ በእንስሳትና ዓሳ ሀብት ልማት ፕሮጀክት (LFSDP) ድጋፍ የተከናወኑና ሌሎች ልማት ስራዎችን እንደሚጎበኙ ከግብርና ሚኒስቴር ማህበራዊ ገጽ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በአኝዋሃ ብሔረሰብ ዞን ያለውን የተፈጥሮ ደን በባዮስፌር ሪዘርቭነት ለማስመዝገብ የሚያስችል ጥናት ተጠናቀቀ
Nov 25, 2023 110
ጋምቤላ፤ ህዳር 15/2016(ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል በአኝዋሃ ብሔረሰብ ዞን ያለውን የተፈጥሮ ደን በባዮስፌር ሪዘርቭነት ለማስመዝገብ የሚያስችል ጥናት መጠናቀቁን የክልሉ አካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ቢሮ አስታወቀ። ደኑን በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት( ዩኔስኮ) በባዮስፌር ሪዘርቭነት ለማስመዝገብ በተካሄደው ጥናት ዙሪያ የባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት የምክክር መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተካሄዷል። የቢሮ ኃላፊዋ ወይዘሮ መሠረት ማቲዎስ በምክክር መድረኩ ላይ እንዳሉት፤ የአኝዋሃ ብሔረሰብ ዞን በተፈጥሮ ሃብት የበለፀገ አካባቢ ነው ብለዋል። ይህንን እምቅ የተፈጥሮ ሃብት በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት( ዩኔስኮ) በባዮስፌር ሪዘርቭነት ለማስመዝገብ ጥናት መጠናቀቁን ተናግረዋል። ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባት ለተጀመረው ጥረት መሳካት በዞኑ ያለውን የተፈጥሮ ደን ማስመዝገብ ጠቀሜታው ጉልህ መሆኑን አብራርተዋል ። ቢሮው የተፈጥሮ ደኑ በድርጅቱ እንዲመዘገብ ለሚደረገው ጥረት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ኃላፊዋ አረጋግጠዋል። የአኝዋሃ ባዮስፌር ሪዘርቭ አጥኚ ድርጅት አማካሪ ፕሮፌሰር ቂጤሳ ሁንዴራ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት የአኝዋሃ ዞን የተፈጥሮ ደን በብዝሃ ሃብቱ እጅግ የበለፀገ ነው ብለዋል። ሃብቱ በድርጅቱ ቢመዘገብ ኢትዮጵያ ያላት የተፈጥሮ ሀብት ተጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ ከማድረግ ባለፈ፤ የጥናትና የምርምር ማዕከል ሆኖ እንዲያገለግል ያስችላል ብለዋል። የአኝዋሃ ባዮስፌር ሪዘርቭ አማካሪ ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ቶሌራ አብርሃም በበኩላቸው ደኑን በድርጅቱ እንዲመዘገብ የሚያደርግ ብዝሃ ህይወት ያለበት አካባቢ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም አካባቢው ከአንድ ሺህ የሚበልጡ የእፅዋትና የተለያዩ እንስሳት ዝርያዎችን በውስጡ አምቆ የያዘ የተፈጥሮ ሃብት መሆኑን ተናግረዋል። የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው የሰው ልጅ አኗኗር ከተፈጥሮ ጋር የተቆራኘ በመሆኑ የተፈጥሮ ሃብቱን በመጠበቅና በመንከባከቡ ረገድ የኅብረተሰቡ ተሳትፎ ወሳኝ ነው ብለዋል። ጥናቱ የተካሄደው ''መልካ ኢትዮጵያ'' የተባለ ሃገር በቀል ድርጅት ከአኝዋሃ ዞን አስተዳደር ጋር በመተባበር መሆኑም ተመላክቷል። ድርጅቱ የማጃንግ የተፈጥሮ ደንን በማጥናት በባዮስፌር ሪዘርቭነት እንዲመዘገብ ማድረጉ ይታወሳል።
በ28ኛው ዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ ኢትዮጵያ የራሷን ተሞክሮዎች ታካፍላለች
Nov 22, 2023 122
አዲስ አበባ፤ ህዳር 12/2016(ኢዜአ)፦በዱባይ በሚካሄደው 28ኛው ዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ ኢትዮጵያ የራሷን ተሞክሮዎች እንደምታካፍል የፕላን እና ልማት ሚኒስቴር ገለጸ። የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ነመራ ገበየሁ፤ በተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ዱባይ ከተማ የሚካሄደውን ዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙኃን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በዚህም ጉባዔው በየዓመቱ የሚካሄድ መሆኑን ገልጸው፤ ለዚሁ የሚሆኑ ዝግጅቶች በመጠናቀቅ ላይ መሆናቸውም ተመላክቷል። ጉባዔው ከኅዳር 20 እስከ ታህሳስ 2 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚካሄድና ከ130 በላይ አገራት በመሪዎች ደረጃ እንደሚሳተፉበት ጠቁመዋል። በጉባዔው በተመረጡ ጉዳዮች ላይ ውይይቶች እንደሚደረጉ፣ አገራት አቋማቸውን እንደሚያሳውቁ እንዲሁም በሁለትዮሽ መድረኮች በርካታ ውይይቶች እንደሚካሄዱ ጠቁመዋል። የድርድር መድረኮችም ሌላኛው የጉባዔው አካል መሆኑን ገልጸው፤ ይህም ትልቁን ቦታ የሚይዝ መሆኑን አመላክተዋል። የፓሪሱ ስምምነት አፈጻጸም ግምገማ የጉባዔው ትልቅ አጀንዳ መሆኑን ገልጸው፤ ይህም ለውሳኔ ሰጪዎች መነሻ እንደሚሆን ይጠበቃል ብለዋል። በፈረንጆቹ አቆጣጠር በ2015 ስምምነት የተደረሰበትን የፓሪሱን አጀንዳ ተፈጻሚ ከማድረግ አኳያ አገራት ምን አከናወኑ? የሚለው በዚሁ መድረክ የሚዳሰስ መሆኑን ጠቁመዋል። ከመደበኛው ውይይቶች ባሻገር ኢትዮጵያ በጉዳዩ ላይ የራሷን ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎች እንዲሁም በተጨባጭ መሬት ላይ እየተተገበሩ ያሉ ሥራዎችን የምታሳይበት መሆኑን አብራርተዋል። በጉባዔው በርካታ ሥራዎችን ለመሥራት መታቀዱን እና ከዚህ ቀደም ከነበሩት መድረኮች በተለየ ትልቅ ዝግጅት መደረጉን ገልፀዋል። ዓለም አቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ የዓለምን የሙቀት መጠን ለመቀነስ ምክክር የሚደረግበት ነው። ጉባዔው መካሄድ ከጀመረ ረዥም ጊዜ ያስቆጠረ ሲሆን፤ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚደርሱ ጉዳቶች መጨመር ለጉባዔው መጀመር ዋንኛው ምክንያት መሆኑ ተጠቅሷል።
በዞኖቹ ባለፉት ዓመታት የተካሄዱት የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እያመጡ ነው
Nov 22, 2023 99
ግምቢ፤ ህዳር 12/2016 (ኢዜአ)፡- በምዕራብና ቄለም ወለጋ ዞኖች ባለፉት ዓመታት በተካሄዱት የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች የመጣው ውጤት ለችግኝ እንክብካቤ እንዳነሳሳቸው የዞኖቹ ነዋሪዎች ገለጹ። በቄለም ወለጋ እና በምዕራብ ወለጋ ዞኖች ባሉ ወረዳዎች ባለፈው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተተከሉ ችግኞች የጥበቃና የእንክብካቤ ስራ እየተከናወነ ነው፡፡ በምዕራብ ወለጋ ዞን በችግኝ እንክብካቤው ተሳታፊ ከሆኑት መካከል የዩብዶ ወረዳ ነዋሪው አቶ ደገፋ ሰንበቶ እንዳሉት በወረዳቸው በየዓመቱ ሀገር በቀል ችግኞች ሲተከሉ ቆይተዋል። የተተከሉ ችግኞች ለታለሙለት ዓላማ እንዲደርሱም "በተከላው መርሃ ግብር እንደተሳተፍን ሁሉ በእንክብካቤውና በጥበቃው ስራ ላይም በመሳተፍ ላይ እንገኛለን" ብለዋል፡፡ "ባለፉት ዓመታት ከተተከሉት ችግኞች የተገኙት ጠቀሜታዎች ለወደፊቱ የበለጠ እንድንተክልና እንድንካባከብ መነሳሳት ፈጥሮልናል" ሲሉም አክለዋል። "ችግኝ መትክል ብቻ ግብ አይደለም" ያሉት ደግሞ በዞኑ የነጆ ወረዳ ነዋሪ አቶ ይፍሩ ዳቃ ናቸው፡፡ "ተፈጥሮ እንክብካቤ ይወዳል" ያሉት ነዋሪው፤ ''ባለፉት ዓመታት የሰራናቸው ስራዎች ውጤቱ አስደሳች መሆኑን ተገንዝበናል አጠናክረን እናስቀጥላለን'' ሲሉም ተናግረዋል። ''በአካባቢያቸው በተተከሉ ችግኞች የደን ሽፋን ጨምሯል፣ የአፈር መራቆትም ቀንሷል'' ያሉት ደግሞ የላሎ አሳቢ ወረዳ ነዋሪ አቶ ያዳታ ሽብሩ ናቸው። በዚህም በመነሳሳት ባለፈው ክረምት የተተከሉ ችግኞችን ለመንከባክብ ከሌሎቹ ነዋሪዎች ጋር በመሳተፍ ላይ መሆናቸውን ነው የተናገሩት። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ፋይሳ ሃምቢሳ በበኩላቸው ባለፈው ክረምት በዞናቸው ከ250 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በተለያዩ መርሃ ግብሮች ተተክለዋል፡፡ ከእነዚህ መካከል 90 በመቶ የሚጠጋ ችግኝ መጽደቁን በባለሙያ በተደረገ ዳሰሳ ለማየት መቻሉንም አክለዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሩን ስኬታማ ለማድረግ ለተተከሉት ችግኞች እየተደረገ ካለው እንክብካቤ ጎን ለጎን ለቀጣዩ የችግኝ ተከላ ስራ የችግኝ ጣቢያዎችን የማዘጋጀትና የዞኑን አርሶ አደሮች በብዛት የማሳተፍ አቅጣጫ ተይዞ እንደሚሰራም ተናግረዋል። በተመሳሳይ በቄለም ወለጋ ዞን ባለፈው ክረምት በተለያዩ መርሃ ግብሮች ለተተከሉ ችግኞች ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍሎችን ያሳተፈ የችግኝ ጥበቃና የመንከባከብ ስራ እየተከናወነ ነው። አርሶ አደሮች፣ የመንግስት ሰራተኞችና ተማሪዎች ደግሞ በእንክብካቤ ስራው ላይ ተሳታፊ ከሆኑት ነዋሪዎች መካከል መሆናቸው ታውቋል። የተተከሉት ችግኞች ጸድቀው የአካባቢን ልምላሜ ሲለውጡ እንደማየት የሚያስደስት ነገር የለም የሚሉት ተሳታፊዎቹ፤ ይህም የበለጠ ለመትከልና የተተከሉትን ለመንከባከብ የሚያነሳሱ መሆናቸውን ተናግረዋል። የቄለም ወለጋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ሙለታ ዋቅጂራ በበኩላቸው በዞኑ ባለፈው ክረምት ከ42 ሚሊዮን በላይ የተለያዩ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በ15 ሺህ 124 ሔክታር መሬት ላይ መተከላቸውን ተናግረዋል፡፡ ከተተከሉት መካከል ከ95 በመቶ በላይ የሚሆኑት መጽደቃቸውን ገልጸው፤ በቀጣይም በዞኑ በ12ቱም ወረዳዎች በህብረተሰቡ ተሳተፎ የጥበቃና የመንከባከብ ስራ እየተከናወነ እንደሆነ አንስተዋል። በኦሮሚያ ክልል ባለፈው ክረምት የተተከሉ ችግኞችን በዘመቻ መልክ የመንከባከብ ስራ ከትናንት ህዳር 11 ጀምሮ እንደሚከናወን የክልሉ ግብርና ቢሮ ማስታወቁን መዘገባችን ይታወሳል።
በምስራቅ ቦረና ዞንና ነቀምቴ ከተማ የችግኝ እንክብካቤ ስራ በመከናወን ላይ ነው
Nov 21, 2023 100
ነገሌ ቦረና/ነቀምቴ ፤ ህዳር 11/2016 (ኢዜአ)፦ የተተከሉት ችግኞች አድገው የድርቅ ተጋላጭነትን ከመቀነስ ባለፈ ለታለመለት ግብ እንዲደርሱ የእንክብካቤ ስራውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የምስራቅ ቦረና ዞንና ነቀምቴ አካባቢ ነዋሪዎች ገለጹ። በምስራቅ ቦረና ዞን የተተከሉት ችግኞች ጸድቀው የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቀነስና ለታለሙለት ግብ እንዲደርሱ በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የአረንጓዴ ልማት ጥበቃና እንክብካቤ ስራ በመከናወን ላይ ነው። በእንክብካቤ ስራው ላይ በመሳተፍ ላይ ካሉት ነዋሪዎች መካከል በዞኑ ሊበን ወረዳ የድቤ ጉቼ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አብዲ ኑር እንዳሉት በግላቸው የተከሉትን ችግኝ በመንከባከብ ላይ ናቸው፡፡ የድርቅ ተጋላጭነትን በዘላቂ ልማት ለመከላከል የተጀመሩት ጥረቶች ጥሩ መሆናቸውን ገልጸው፤ ችግኝ መትከል ብቻውን ለውጤት እንደማያበቃም ተናግረዋል፡፡ "ልማቱ ለውጤት እስኪበቃ መንከባከብ፣ ውሃ ማጠጣት፣ መኮትኮትና ከእንስሳት ንክኪ መጠበቅ የእለት ተእለት የስራችን አካል ሊሆን ይገባል፤ ተግባራዊም እያደረግን ነው" ብለዋል፡፡ የዚሁ ወረዳና ቀበሌ ነዋሪ አቶ መሐመድ አልዪና 30 ባልደረቦቻቸው ባለፉት ዓመታት በጋራ የተከሉት ችግኝ ብዛት 500 መድረሱንና ጸድቆ በጥሩ ቁመና ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ አምናም በተመሳሳይ መልኩ የተከሉትን 50 የሀበሻ ጽድና ግራቪሊያ የመሳሰሉት ችግኝ ለታሰበለት ውጤት ለማብቃት በመንከባከብ ላይ ነን መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በዞኑ ባለፈው ዓመት ከመጋቢት አጋማሽ እስከ ነሐሴ መጨረሻ ከተተከለው ውስጥ ከ78 በመቶ በላይ ችግኝ መጽደቁን የገለጸው ደግሞ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ነው፡፡ የጽህፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ መስቀሉ ቱሉ በዞኑ የድርቅ ተጋላጭነትን ከመከላከል ያለፈ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው 28 ነጥብ 5 ሚሊዮን ችግኝ መተከላቸውንም አስታውሰዋል፡፡ ከተተከሉት ችግኞች መካከል የሀበሻ ጽድ፣ ግራቪሊያ፣ ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ኮሶ፣ ሙዝ፣ አቦጋዶ፣ ማንጎና ፓፓያ ዋና ዋናዎቹ እንደሆኑ ጠቅሰው፤ በዞኑ በተደረገ እስካሁን 22 ሚሊዮን 5 ሺህ በላይ ችግኝ እንደጸደቀ በባለሙያዎች የመስክ ምልከታ አረጋግጠናል ብለዋል፡፡ ድርቅን በዘላቂነት ለመከላከልም በዞኑ የተጀመረውን የችግኝ ልማት ጥበቃና እንክብካቤ ስራ አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል። በተመሳሳይ በነቀምቴ ከተማ ባለፈው ክረምት ለተተከሉ ችግኞች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያሳተፈ የእንክብካቤ ስራ እየተከናወነ ነው። በችግኝ ተከላው ላይ የተሳተፉት አርሶ አደሮችና የመንግስት ሰራተኞች እንዳሉት የተከሉት ችግኝ ከግብ ደርሶ የሚፈለገውን ጠቀሜታ እንዲያሳካ የጀመሩትን የእንክብካቤ ስራ በትኩረት እንደሚሰሩ ተናግረዋል። "በመትከል ብቻ ሳይሆን በመንከባከብ ልምላሜን ለነገ ትውልድ ማውረስ ይኖርብናል" ያሉት የዘመቻው ተሳታፊዎች፤ "ችግኝን ካልተንከባከብን የምንፈልገውን ውጤት ማግኘት አንችልም" ብለዋል። ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ትግስት ሃምቢሳ እንዳሉት "የዛፍ ችግኝ እንደ ህፃናት ትኩረት ይሻሉ" ይላሉ። በመሆኑም አስፈላጊውን እንክብካቤ በማድረግ ለከተማው ውበትና ለሌሎች ጠቀሜታ ማድረስ ይገባል ብለዋል። የነቀምቴ ከተማ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ግርማ ከድር እንደተናገሩት ባለፈው ዓመት በከተማዋ ከተተከሉት ከ 2 ሚሊዮን 180 ሺህ በላይ ችግኞች 85 በመቶው መፅደቅ ችለዋል። በከተማዋ እና አካባቢዋ የተተከሉትን ችግኞች በሚገባ በመንከባከብ ላይ መሆናቸውን አክለዋል። በእንክብካቤው ላይ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችን ጨምሮ ተማሪዎች፣ የመንግስት ሰራተኞች፣ የአካባቢው ነዋሪዎች እና አርሶ አደሮች ተሳትፈዋል። በኦሮሚያ ክልል ባለፈው ክረምት የተተከሉ ችግኞችን በዘመቻ መልክ የመንከባከብ ስራ ከዛሬ ህዳር 11 ቀን 2016ዓ.ም ጀምሮ እንደሚከናወን የክልሉ ግብርና ቢሮ ማስታወቁን መዘገባችን ይታወሳል።
ኢትዮጵያ "የሬድ ፕላስ" ምዕራፍ ሁለት የደን ልማት የኢንቨስትመንት ፕሮግራምን ይፋ አደረገች
Nov 17, 2023 344
አዲስ አበባ፤ ህዳር 7/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በ40 ሚሊዮን ዶላር የሚተገበር "የሬድ ፕላስ" ምዕራፍ ሁለት የደን ልማት የኢንቨስትመንት ፕሮግራምን ይፋ አደረገች። ኢትዮጵያ በደን ልማትና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ላይ እያደረገች ያለውን ጥረት ዓለምአቀፉ ማህበረሰብ እንዲደግፍ የግብርና ሚኒስቴር ጠይቋል። በመርኃ ግብሩ ላይ የግብርና ሚኒስትር ዶክተር ግርማ አመንቴ፣ በኢትዮጵያ የኖርዌይ አምባሳደር ስቴይን ክሪስቴንሰን፣ የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር ከበደ ይማምና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል። የግብርና ሚኒስትር ዶክተር ግርማ አመንቴ እንዳሉት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር 32 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኞች ተተክለዋል። ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያደርሰውን ተፅዕኖ ለመቋቋም የሚደረገውን ጥረት እየደገፈች መሆኗንና ለዚህም የተለያዩ ስትራቴጂዎችን ቀርፃ እየተገበረች መሆኑን ተናግረዋል። የሬድ ፕላስ የደን ልማት የመጀመሪያው ምዕራፍ መርኃ ግብርም በምግብ፣ በብዝሃ ህይወትና ሌሎችም ዘርፍች ውጤት መምጣቱን ገልጸው፤ በሁለተኛው ምዕራፍም የላቀ ውጤት ይጠበቃል ብለዋል። በደን ልማት እንክብካቤ ስራዎች ላይ የአጋር አካላት አስተዋፅኦ ከፍተኛ ሚና እንዳለው በማንሳት፤ በዚህ ረገድ የኖርዌይ መንግስት እያበረከተ ያለው አስተዋጽኦ ለሌሎች አገራት ምሳሌ እንደሆነ አንስተዋል። መንግስት ለፕሮግራሙ አተገባበር አስፈላጊውን እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸው፤ ሌሎች አካላትም በደን ልማት ላይ የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል። የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር ከበደ ይማም ሁለቱ አገራት ከ1947 የጀመረ ወዳጅነት እንዳላቸው በማስታወስ የኖርዌይ መንግስት ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር ሲሰራባቸው ከቆዩ ጉዳዮች መካከል የአየር ንብረት ለውጥ አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል። የኖርዌይ መንግስት የፕሮጀክቱን የመጀመሪያ ምዕራፍ ትግበራ ሲደግፍ እንደነበር በማስታወስ፤ ይህም የተጎዱ መሬቶችን በደን በመሸፈን እንዲያገግሙ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የኖርዌይ አምባሳደር ስቴይን ክሪስቴንሰን በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የምታደርገውን ጥረት እየደገፈን ነው ብለዋል። ሁለቱ አገራት በአየር ንብረት ዙሪያ በትብብር ለመስራት ከ10 ዓመት በፊት ስምምነት ማድረጋቸውን በማስታወስ፤ የኖርዌይ መንግስት በኢትዮጵያ የደን ልማት ስራን ለመደገፍ እስካሁን 130 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማድረጉን ገልጸዋል። "የብሄራዊ ሬድ ፕላስ" ፕሮግራም አስተባባሪ ዶክተር ይተብቱ ሞገስ እንዳሉት፤ ከፈረንጆቹ 2017 ጀምሮ የሬድ ፕላስ ምዕራፍ አንድ በኖርዌይ መንግስትና በሌሎች አጋር አካላት ድጋፍ መተግበሩን ተናግረዋል። የኖርዌይ መንግስት ለመጀመሪያው ምዕራፍ ትግበራ የ75 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማድረጉን አንስተው ይህም ህብረተሰቡን ያሳተፈ የደን አስተዳደር ለመዘርጋት ያስቻለ መሆኑን ገልፀዋል። በዚህም አንድ ሚሊዮን ሄክታር የሚጠጋ መሬት እንዲያገግም፣ ወደ ደን እንዲለወጥና እንዲለማ መደረጉ፣ የህብረተሰቡን ህይወት የሚያሻሽሉ የተለያዩ የገጠር ልማት ስራዎች መሰራታቸውንም ነው ያስረዱት። ለሶስት ዓመታት በሚተገበረው ምዕራፍ ሁለት "የሬድ ፕላስ" ትግበራ 40 ሚሊዮን ዶላር የሚያስፈልግ ሲሆን፤ ኖርዌይ 25 ሚሊየን ዶላር ድጋፍ ማድረጓን ጠቅሰዋል። በቀጣይ የሬድ ፕላስ ብሔራዊ የደን ልማት ፕሮግራምን ወደ ካርቦን ገበያ ስርዓት በማስገባት ፕሮግራሙን በራሱ ገቢ በቀጣይነት ለመተግበር ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩ በዓለም አቀፍ ደረጃ በካርቦን ልቀት ቅነሳ ያመጣው ውጤት ተመዝኖ አገሪቱ ክፍያ እንድታገኝ እገዛ የሚያደርግ መሆኑን አንስተዋል። "የሬድ ፕላስ" የምዕራፍ አንድ ፕሮግራም በኢትዮጵያ የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ ለማስቻል ላለፉት አምስት አመታት ሲተገበር ቆይቷል።
ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ ቅነሳ መርሐ ግብሯ የሴቶችን ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራትን አጠናክራ ትቀጥላለች - አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ
Nov 13, 2023 172
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተፅዕኖን ለመቀነስ እያደረገች ባለው ጥረት የሴቶችን የመሪነት ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራትን አጠናክራ እንደምትቀጥል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከዩኔስኮ እና በኢትዮጵያ ከተባበሩት አረብ ኢምሬቶች ኤምባሲ ጋር የሴቶች ተሳትፎ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ያለውን ሚና በተመለከተ ውይይት አካሂደዋል፡፡ የአየር ንብረት ለውጥ በሚያሳድረው ተጽዕኖ ለድህነትና ለችግር ከተጋለጠው የዓለም ህዝብ መካከል 60 በመቶ ሚሆኑት ሴቶች ሲሆኑ በተፅዕኖው ከሚፈናቀሉ መካከል 80 በመቶዎቹ ሴቶች መሆናቸውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት መረጃ ያሳያል። አፍሪካ ወደ ከባቢ አየር የምትለቀው የበካይ ጋዝ መጠን ዝቅተኛ ቢሆንም በአየር ንብረት ለውጥ የሚደርስባት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳት ከሁሉም የላቀ ነው፡፡ እንደ አህጉር 70 በመቶ የሚሆነው የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ የሚስተናገደው በግብርናው ዘርፍ ላይ ሲሆን ከሰሀራ በታች ባሉ ሀገሮች ደግሞ የከፋ እንደሆነ ይገለፃል፡፡ በዚሁ ቀጣና ባሉ ሀገራት ከሚኖሩ ሴቶች 60 በመቶዎቹ በአየር ንብረት ለውጥ እየተጎዳ በሚገኘው የግብርናው ዘርፍ የሚሰሩ ሲሆን 70 በመቶውን የምግብ ፍጆታ የማምረት ጫናን የተሸከሙ ናቸው። የአየር ንብረት ለውጥም በእነዚሁ ሴቶች ላይ የከፋ ጫና እያሳደረ መሆኑ ይነገራል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ በውይይቱ ላይ እንዳሉት፤ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም የሴቶች ሚና የጎላ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተለያዩ አገልግሎት የሚውሉ ከ32 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን ስትተክል ሴቶች አስተዋፅኦ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። የአየር ንብረት ለውጥን በመቋቋም ቀጣይነት ያለው ኢኮኖሚያዊ እድገት ለማምጣትና በዓለም ነባራዊ ሁኔታ ላይ ለውጥ ለማምጣት ሴቶችን በሚገባ ማብቃት ለነገ የማይባል ጉዳይ ነው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም በምታከናውናቸው ዘርፈ ብዙ ተግባራት ላይ የሴቶችን ሚናና ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ የጀመረችውን ስራ አጠናከራ እንደምትቀጥል ጠቁመዋል፡፡ በኢትዮጵያና አፍሪካ ህብረት የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ኤምባሲ ተወካይ ሳኦድ አል ታኒጂ፤ ሀገራቸው በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ፕሮጀክት ላይ የሴቶችን ሚና ለማሳደግ ቁርጠኛ መሆኗን ገልጸዋል፡፡ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ሴቶች በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ መቋቋም፤ በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና መሰል ዘርፎች ላይ የላቀ ሚና እንዲኖራቸው እድል ትሰጣለች ብለዋል፡፡ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት /ዩኔስኮ/ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ዶክተር ሪታ ቢሱናት በዓለም ላይ ደረጃው ይለያይ እንጂ ሴቶች የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ተጎጂዎች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በአፍሪካ ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት የሴቶችን ሁለንተናዊ ተሳትፎ ማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ለሴቶች የሚሰጣቸው ውክልና ዝቅተኛ ነው ያሉት ዳይሬክተሯ፤ በመሆኑም የሴቶችን አካታችነት፣ ውሳኔ ሰጭነትና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራትን ማከናወን የግድ ነው ብለዋል፡፡ ዩኔስኮ የሴቶችን የመሪነትና ውሳኔ ሰጭነት ሚና ለማሳደግ ከመንግስትና ከዘርፉ ተዋንያን ጋር በትብብር ለመስራት ሁልጊዜም ዝግጁ ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ የ "ታላቁ አረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭ" ብሔራዊ ጥምረት በይፋ አቋቋመች
Nov 8, 2023 261
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 28/2016 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ የታላቁ አረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭን በተቀናጀ አግባብ መምራት የሚያስችላትን ብሔራዊ ጥምረት ዛሬ በይፋ አቋቋመች፡፡ እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር በ2007 ይፋ የሆነው ታላቁ አረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭ፤ በረሀማነትን ለመከላከል 8 ሺህ ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ደን በሳሄል ቀጣና ለመትከል ያለመ ግዙፍ አህጉራዊ ፕሮጀክት ነው። የኢንሼቲቩን አስመልክቶ የተዘጋጀ ውይይት ዛሬ በአፍሪካ ሕብረት የመሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሄዷል። ኢትዮጵያም ኢንሼቲቩን ከመሰረቱና ስምምነቱን ከፈረሙ 11 የአፍሪካ አገራት አንዷ ስትሆን፤ በዛሬው መድረክም ኢኒሼቲቩን በተቀናጀ አግባብ መምራት የሚያስችላትን ብሔራዊ ጥምረት አቋቁማለች። ጥምረቱ የፌደራልና የክልል መንግስታት እንዲሁም ተቋማት፣ ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ የልማት አጋሮችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላትን ያካተተ ነው፡፡ በዚህም ጥምረቱ ትግበራውን ወጥ የማድረግና ለዚህም የሚያስፈልገውን ሀብት በተቀናጀ መልኩ የማሰባሰብ ኃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ የኢትዮጵያ ደን ልማት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሞቱማ ቶሌራ ኢትዮጵያ ኢኒሼቲቩን በአማራ፣ ትግራይና አፋር ክልሎች በሚገኙ 58 ወረዳዎች እየተገበረች እንደምትገኝ ገልጸዋል። ትግበራው በተለያዩ ምክንያቶች በወረዳዎቹ የተራቆተውን 13 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ዳግም በደን የመሸፈን ዓላማ እንዳለው አመልክተዋል። መርሐ ግብሩ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከልና ለደን ልማት ስራዎች ጉልህ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም ኢኒሺዬቲቩ ኢትዮጵያ በአገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ደረጃ እየተገበረቻቸው ላሉ የአየር ንብረት ለውጥ ማዕቀፎች ትግበራ አበርክቶ እንደሚኖረውም ነው ዶክተር ሞቱማ ያስረዱት። ኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን ለመቋቋም የሚያስችሉ እርምጃዎችን እየወሰደች እንደምትገኝ አመልክተዋል። ከዚህም አንጻር ኢኒሼቲቩ በኢትዮጵያ እየተከናወኑ ያሉ የአረንጓዴ ልማት ስራዎች ጋር የሚተሳሰር እንደሆነ በማንሳት። በመሆኑም ዓለም አቀፍ አጋሮች ለትግበራው አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርጉም ጥሪ አቅርበዋል። በአፍሪካ ሕብረት የ"ታላቁ የአፍሪካ አረንጓዴ ግንብ ኢንሼቲቭ" አስተባባሪ ዶክተር ኤልቪስ ፖል ኢኒሼቲቩ አህጉሪቷ በአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖ ዘላቂ ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል የፓን አፍሪካ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ አኳያ ኢትዮጵያ የተራቆተ መሬትን መልሶ በደን መሸፈን እያከናወነች ያለችው ተግባር ለሌሎች አፍሪካ አገራት ምሳሌ የሚሆን ነው ብለዋል። በመሆኑም አህጉራዊው ተቋም ለኢትዮጵያ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አመልክተዋል። በተባበሩት መንግስታት ድርጅት በረሃማነትን የመከላከል ማዕቀፍ(UNCCD) የ"ታላቁ የአፍሪካ አረንጓዴ ግንብ ኢንሼቲቭ" ፕሮግራም ዳይሬክተር ዶክተር ቢርጊ ላሚዛና በበኩላቸው ኢትዮጵያ ለኢኒሼቲቩ ትግበራ የሚያስፈልገውን ብሔራዊ ጥምረት ያቋቋመች 10ኛዋ አፍሪካዊት አገር መሆኗን ጠቁመዋል። ጥምረቱ ለኢኒሼቲቩ ትግበራ የጋራ አቅም ከማሰባሰብና ትብብር ከመፍጠር አኳያ ወሳኝ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። ዓለም አቀፍ አጋሮችም ለመርሐ ግብሩ ትግበራ የገቡትን ቃል እንዲፈጽሙ ጥሪ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ የደን ልማት "የታላቁ አረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭ" አፈጻጸምና የብሔራዊ ጥምረቱን አስመልክቶ የመነሻ ጽሁፍ አቅርቦ ውይይት ተደርጎበታል። ብሔራዊ ጥምረቱ የዝግጅት ስራዎቹን አጠናቆ በቀጣይ ሳምንታት ወደ ስራ እንደሚገባ በመድረኩ ላይ ተገልጿል። በስብስባው የኢትዮጵያ ደን ልማት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሞቱማ ቶሌራ፣ የአፍሪካ ሕብረት ግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽን ተወካዮች ፣የደን ልማት፣ አካባቢ ጥበቃና አረንጓዴ ልማት ላይ የሚሰሩ አገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል። የ"ታላቁ አረንጓዴ ግንብ ኢኒሼቲቭ" ኢትዮጵያን ጨምሮ በ22 የአፍሪካ አገራት እየተተገበረ የሚገኝ ሲሆን በአህጉሪቷ የተራቆተ 100 ሚሊዮን ሄክታር መሬት መልሶ በደን የመሸፈን ግብ ያለው ፕሮጀክት ነው።
ኢትዮጵያ ብዝሃ ህይወትን በመጠበቅ ረገድ አብነት የሚሆን ተግባር እያከናወነች ነው
Nov 8, 2023 184
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 28/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ብዝሃ ህይወትን በመጠበቅ ረገድ አብነት የሚሆን ተግባር እያከናወነች መሆኑ ተገለጸ፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካ ቀንድ አካባቢ ማዕከልና ኔትዎርክ ድርጅት የብዝሃ-ህይወት ጥበቃን የተመለከተ የመጀመሪያው የምስራቅ አፍሪካ ቀጠና አውደ ጥናት በአዲስ አበባ እያካሄደ ነው፡፡ የአውደ ጥናቱ ዋና ዓላማ ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ ጥናቶችን ማቅረብ ሲሆን፤ ከበርካታ የአፍሪካ አገራት የመጡ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአፍሪካ ቀንድ የአካባቢ ማዕከልና ኔትዎርክ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ፕሮፌሰር መኩሪያ አርጋው፤ በአውደ ጥናቱ የአገራት ልምድና ተሞክሮ እንደሚቀርብ ጠቁመዋል፡፡ ይህም አገራት ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ ሃሰቦችን እንዲወስዱ ትልቅ እድል እንደሚፈጥር አብራርተዋል፡፡ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤሊያስ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የተፈጥሮ ሃብትና ብዝሃ ህይወትን ለመጠበቅ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ለአብነትም በአገር አቀፍ ደረጃ እየተከናወኑ ያሉ የአረንጓዴ አሻራ እንዲሁም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን አንስተዋል፡፡ በዚህም አከባቢና ብዝሃ ህይወትን ከመጠበቅ ባለፈ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡ በአውደ ጥናቱም ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ፣ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ እና በሌሎችም ዘርፎች ያከናወነቻቸውን ስራዎች በተሞክሮነት እንደምታቀርብም ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ኢትዮጵያ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ እያከናወነች ያለውን ተግባርም ከአምስት የአፍሪካ አገራት ለተወጣጡ ልዑካን ቡድኖች ልምድ ማካፈሏን ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካን አንድ ሶስተኛ የሚሆን ብዝሃ-ህይወት ክምችት አላት ያሉት ደግሞ የኢትዮጵያ ብዝሀ ህይወት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር መለሰ ማሪዮ ናቸው፡፡ ለአብነትም ከ90 ሺህ በላይ የብዝሃ ህይወት ናሙናዎች ተጠብቀው እንደሚገኙም ጠቁመዋል፡፡ እነዚህም የአየር ንብረት ለውጡን ተቋቁመው ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ለሚሆኑ የምርመር ስራዎች ፋይዳቸው የጎላ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ በአውደ ጥናቱ በመሳተፍ ላይ የሚገኙት ዓለም አቀፍ የብዝሃ ህይወት እና የስነ-ምህዳር አገልግሎቶች ተቋም አስተባባሪ ዶክተር ሄኒንግ ሶመር፤ ተቋሙ አገራት በዕውቀት ላይ የተመሰረተ የብዝሃ ህይወት እና ስነምህዳር ጠበቃ እንዲያከነወኑ ድጋፍ እንደሚያደርግ ጠቁመዋል፡፡ በቀጣይም አገራት ለብዝሃ-ህይወት እና ስነ-ምህዳር አያያዝ ትኩረት በመስጠት የአየር ንብረት ለውጥን ሊከላከሉ እንደሚገባም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ አውደ ጥናቱ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ሲሆን የተለያዩ አገራት ተሞክሮን የያዙ ጥናታዊ ጽሁፎች እንደሚቀርቡም ተገልጿል፡፡
የ"ታላቁ የአፍሪካ አረንጓዴ ግንብ ኢንሼቲቭ" አፈጻጸም ላይ ትኩረት ያደረገ ስብስባ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው
Nov 8, 2023 174
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 28/2016 (ኢዜአ)፦ የ"ታላቁ የአፍሪካ አረንጓዴ ግንብ ኢንሼቲቭ" አፈጻጸም የሚገመግም ስብስባ በአፍሪካ ሕብረት የመሰብሰቢያ አዳራሽ በመካሄድ ላይ ይገኛል። “ታላቁ የአፍሪካ አረንጓዴ ግንብ ኢንሼቲቭ" በረሀማነትን ለመከላከል 8 ሺህ ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ደን በሳሄል ቀጣና ለመትከል ያለመ ግዙፍ ፕሮጀክት ነው። በስብስባው የኢትዮጵያ ደን ልማት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሞቱማ ቶሌራ፣የአፍሪካ ሕብረት ግብርና፣ገጠር ልማት፣ብሉ ኢኮኖሚና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽን ተወካዮች፣የደን ልማት፣አካባቢ ጥበቃና አረንጓዴ ልማት ላይ የሚሰሩ አገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል። ከአፍሪካ ሕብረት ዋነኛ ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ የሆነው ይህ ኢንሸቲቭ እንደ አውሮፓዊያን አቆጣጠር በ2007 የተጀመረ ሲሆን፤ ዓላማውም የሰሃራ በረሃ መስፋፋትን ለመከላከልና በቀጣናው የሚገኙ አገራትን ኢኮኖሚ ማሻሻል እንደሆነ ተገልጿል። ለኢኒሼቲቩ ተፈጻሚነት የልማት አጋሮች፣ዓለም አቀፍ ተቋማትና የተለያዩ አገራት የገንዘብ ድጋፍ እያደረጉ መሆኑም ተገልጿል፡፡ ኢትዮጵያም ኢኒሼቲቩን ከመሰረቱና ስምምነቱን ከፈረሙ የአፍሪካ አገራት መካከል አንዷ ስትሆን፤ በአማራ፣ትግራይና አፋር ክልሎች በሚገኙ 58 ወረዳዎች እየተገበረችው ትገኛለች፡፡ በወረዳዎቹ እየተከናወነ ያለው ስራ 13 ሄክታር የተራቆተ መሬት በደን መልሶ ለመሸፈን የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል።
የአየር ንብረት ለውጥ ሊያስከትል የሚችለውን ተፅዕኖ በዘላቂነት ለመቋቋም ብሔራዊ የአየር ጠባይ አገልግሎት ማዕቀፍን መተግበር ይገባል
Oct 28, 2023 418
አዳማ ፤ ጥቅምት 17/2016 (ኢዜአ)፡- የአየር ንብረት ለውጥ ሊያስከትል የሚችለውን ተፅዕኖ በዘላቂነት ለመቋቋም የሚያስችል ብሔራዊ የአየር ጠባይ አገልግሎት ማዕቀፍን በየደረጃው ባለ መዋቅር በአግባቡ መተግበር እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢታፋ አስገነዘቡ። የአየር ጠባይ አገልግሎት ማዕቀፍን ለማፅደቅና ወደ ክልሎች በማውረድ ተፈፃሚ ለማድረግ ያለመ የሁሉም ክልሎች ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበት መድረክ በአዳማ በመካሄድ ላይ ይገኛል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢታፋ እንደገለፁት በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ምክንያት ድርቅና ጎርፍ በተደጋጋሚ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ በሀገሪቱ፣ አንዳንድ አካባቢዎች ከባለፉት ዓመታት ጀምሮ አሁንም ድረስ ድርቅና ጎርፍ በእንስሳትና ሰብል ልማት ላይ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ተናግረዋል። የአየር ንብረት ለውጥ እያስከተለ ያለውን ተፅዕኖ በዘላቂነት ለመቋቋም ብሔራዊ የአየር ጠባይ አገልግሎት ማዕቀፍ መዘጋጀቱንም ገልፀዋል። በዚህም ማዕቀፉ በሁሉም ክልሎች በየደረጃው ባሉ የአየር ጠባይ አገልግሎት ተጠቃሚዎች የሚተገበር መሆኑን ጠቅሰው በተለይ ግብርና ፣ ውሃ፣ ጤና፣ ትምህርትና የእንስሳት ሀብት፣ የአካባቢ ጥበቃ ባለድርሻ አካላት በቅንጅት መተግበር አለባቸው ብለዋል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የአየር ጠባይ መረጃን በጥራት መሰብሰብ ፣ መተንተን ፣ ማደራጀትና ማሰራጨት እንደሚገባው አስገንዝበዋል። የአገልግሎት ማዕቀፉ በተለይ ጎርፍና ድርቅን ጨምሮ ወቅቱን ባልጠበቀው ዝናብ የሚከሰቱ ችግሮችን ለመከላከል ከተፈጥሮ ዝናብ ጥገኝነት ለመላቀቅ የሚደረገው የመስኖ ልማት ስራ ስኬታማ እንዲሆን የዝናብ ውሃን ጨምሮ የገፀ ምድርና ከርሰ ምድር ውሃ በአግባቡ እንዲለማ የሚያስችል ግብዓትና መረጃ የሚገኝበት የአሰራር ስርዓት መሆኑንም አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ እንደገለፁት ኢንስቲትዩቱ ሀገሪቷ እያከናወነች ያለችውን ልማትና ዕድገት ማገዝ የሚችል የአየር ጠባይ ትንበያ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ብሔራዊ የአየር ጠባይ አገልግሎት ማዕቀፍን ፣ ከአየር ጠባይ ትንበያ አገልግሎት ጋር በጋራ የአሰራር ስርዓቱን በውጤታማነት ለመተግበር ነው ብለዋል። የአየር ጠባይ አገልግሎት ተጠቃሚዎችም ሳይንሳዊ የሆነ ጥራት ያለው የአየር ጠባይ መረጃ ተደራሽ ለማድረግም የአሰራር ስርአት ማእቀፍ ማስፈለጉንም ተናግረዋል፡፡ በመድረኩ ላይ ከውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ፣ከፌዴራልና ክልል ግብርና ሴክተሮች፣ከክልሎች አካባቢ ጥበቃና ከአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽኖች የተወጣጡ አመራሮችና የስራ ሃላፊዎች ተሳታፊ ሆኖዋል።
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ለአካባቢ ጥበቃ የሰጠችው ትኩረት የሚደነቅ ነው- በኢትዮጵያ የቼክ ሪፐብሊክ አምባሳደር
Oct 25, 2023 273
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 14/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለአካባቢ ጥበቃ የሰጠችው ትኩረት በምሳሌነት የሚጠቀስና የሚደነቅ መሆኑን በኢትዮጵያ የቼክ ሪፐብሊክ አምባሳደር ሚሮስላቭ ኮሴክ ገለጹ። የቼክ ሪፐብሊክ የልማት ትብብር የአየር ንብረት ለውጥ መከላከልን በተመለከተ ከተለያዩ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆነ ተቋማት ጋር በአዲስ አበባ ውይይት አካሂዷል። በመድረኩ ላይ የተገኙት በኢትዮጵያ የቼክ ሪፐብሊክ አምባሳደር ሚሮስላቭ ኮሴክ፤ የአየር ንብረት ለውጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ፈተና ሆኖ መቀጠሉን ገልጸዋል። በተለይም በአፍሪካ ተጽዕኖው ከፍተኛ መሆኑን የጠቀሱት አምባሳደሩ ለድርቅ፣ ጎርፍ፣ የመሬት መንሸራተትና ለሌሎች ተያያዥ ችግሮች ማጋለጡን አብራርተዋል። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለአካባቢ ጥበቃ የሰጠችው ትኩረት በምሳሌነት የሚጠቀስና የሚደነቅ መሆኑን ገልጸው ችግሩን ለመከላከልና ተጨባጭ ለውጥ ለማምጣት የአገራት ትብብር አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የሀገራትና የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን ርብርብ የሚጠይቅ በመሆኑ የዓለም ልዩ ትኩረት ሆኖ ለጋራ መፈትሄ መስራት ይጠይቃል ብለዋል። የዓለም አቀፉ የአረንጓዴ ልማት ኢንስቲትዩት የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ዳንኤል ጎቦናያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የጋራ ምላሽ ይፈልጋል ብለዋል። ከዚህ አንጻር ኢትዮጵያ ለአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የሰጠችው ትኩረት የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን ለመከላከል ለሚደረገው ጥረት አጋዥ መሆኑን ጠቅሰዋል። በመድረኩ ቼክ ሪፐብሊክ በኢትዮጵያ የአየር ንብረት ተጽዕኖ መቋቋም የሚያስችል የግብርና ልማት እንዲስፋፋና የአረንጓዴ ልማት እንዲጠናከር እየሰራች መሆኑ ተመላክቷል።
የመንግስታቱ ድርጅት እየተለወጠ ያለውን የዓለም ሁኔታ ያማከለ ፍትሐዊ ተቋማዊ ማሻሻያ ማድረግ ይኖርበታል - አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ
Oct 24, 2023 280
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 13/2016 (ኢዜአ)፦ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በፍጥነት እየተለወጠ ከሚገኘው የዓለም ሁኔታ ጋር የሚራመድ ሁሉን አቃፊና ፍትሐዊ ተቋማዊ ማሻሻያ ማድረግ እንደሚገባው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ ገለጹ። ማሻሻያው አፍሪካን ጨምሮ ሌሎች በማደግ ላይ የሚገኙ አገራትን ከግምት ውስጥ ያስገባ መሆን አለበትም ብለዋል። የ2023 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቀን "የአየር ንብረት ለውጥ እርምጃ አውደ ግንባሮች" በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዛሬ ተከብሯል። በመርሃ-ግብሩ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ፣ የተለያዩ አገራት አምባሳደሮች፣ የዓለም አቀፍ ተቋማት የስራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። ኢትዮጵያ የተመድ መስራች አባል አገርና ከድርጅቱ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ጋር ስድስት አስርት ዓመታትን ያስቆጠረ ፍሬያማ የትብብር ታሪክ እንዳላት አምባሳደር ምስጋኑ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ኮሚሽኑ ዋና መቀመጫው አዲስ አበባ እንዲሆን በተደረገበት ታሪካዊ ውሳኔ የነበራት አስተዋጽኦ የአፍሪካን ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት ከማስተዋወቅ አንጻር ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን አመልክተዋል። ዓለም በአሁኑ ሰዓት በፈጣን ሁኔታ ለውጦችን እያስተናገደች እንደምትገኝና ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲውም በተለዋዋጭ ሁኔታዎች እያለፈ ይገኛል ብለዋል። ተመድ የዓለምን አሁናዊ ነባራዊ እውነታ ከግምት ውስጥ ያስገባ ፍትሐዊና ሁሉን አሳታፊ ተቋማዊ ማሻሻያ በማድረግ አፋጣኝ ምላሽ መስጠት እንዳለበት ነው አምባሳደር ምስጋኑ የገለጹት። ድርጅቱ በባለብዙ ወገን የዲፕሎማሲ ስራው የአፍሪካና በማደግ ላይ የሚገኙ አገራትን ፍላጎትና ድምጽ ማካተት እንደሚኖርበትም አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ ለዓለም አቀፍ የባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲ ስርዓት መጎልበት የምታደርገውን ጥረት አጠናክራ እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል። ተመድ ኢትዮጵያ እየተገበረች ላለችው የ10 ዓመት መሪ የልማት እቅድና በአገሪቱ እየተከናወኑ ላሉ የልማት ስራዎች የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥል አምባሳደሩ ጥሪ አቅርበዋል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር ዶክተር ሞኒክ ንሳንዛባጋንዋ፤ በአህጉሪቱና በተለያዩ ዓለማት የሚከሰቱ ፈተናዎችን ምላሽ ለመስጠት በትብብር መስራት ይጠይቃል ብለዋል። የስርዓተ ጾታ እኩልነት፣ ነፃነትና ፍትሕዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኢኮኖሚ ሥርዓት መገንባት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል። የአፍሪካን ቀጣይነት ያለው ደህንነትና ኢኮኖሚያዊ እድገት ለማስቀጠል ለፈጠራ ስራዎች ትኩረት መስጠት ይኖርብናልን ነው ያሉት። የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ተጠባባቂ ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ፔድሮ፤ ዘላቂ ሰላምና ልማትን በማረጋገጥ ለዜጎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በትኩረት መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል። የተመድ ቻርተር ዲፕሎማሲያዊ ትብብርን ለማስፋት የሚያስችሉ መርሆዎችን መያዙን ጠቅሰው የትብብር እድሎችን በማስፋት ለሴቶች ተጠቃሚነት መስራት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ቀን ድርጅቱ እ.አ.አ 1971 ባሳለፈው የውሳኔ ሀሳብ ቁጥር 2782 አማካኝነት በየዓመቱ በተመድ አባል አገራት እየተከበረ ይገኛል። ቀኑ እ.አ.አ የተቋቋመውን 1945 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ምስረታ በማሰብ የሚከበር ነው።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የደቡብ አጋማሽ የሀገሪቱ ክፍሎች ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ሊኖር ይችላል- የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት
Oct 12, 2023 367
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 1/2016 (ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የደቡብ አጋማሽ የሀገሪቱ ክፍሎች ላይ የተስፋፋና ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ሊኖር እንደሚችል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ በሚቀጥሉት አሥር ቀናት ዝናብ ሰጭ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች በአብዛኛው በደቡብና በደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች የተሻለ ገጽታ ይኖራቸዋል። ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው የሆኑ የደቡብ አጋማሽ የሀገሪቱ ክፍሎች ላይ የተስፋፋና ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ሊኖር አንደሚችልም አመላክቷል። በመካከለኛው፣ በምስራቅና በሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች ከሚጠናከሩት የአየር ሁኔታ ክስተቶች ላይ በመነሳት ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብ ሊኖር እንደሚችልም ጠቁሟል። ከኦሮሚያ ክልል ሁሉም የወለጋ ዞኖች፣ ጅማ፣ ኢሉባቦር፣ ቡኖ በደሌ፣ ሁሉም የአርሲ፣ የባሌና የጉጂ ዞኖች፣ ምስራቅና ምዕራብ ሐረርጌና የቦረና ዞን ከመደበኛ በላይ ዝናብ ሊኖራቸው ይችላል። ከአማራ ክልል ምዕራብ ጎጃም፡ መካከለኛው የሰሜንና የምዕራብ ጎንደር፣ የባህር ዳር ዙሪያ፣ አዊ ዞንም እንዲሁ። የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ዞኖች፤ የሲዳማ ክልል ዞኖች፤ የመካከለኛው ኢትዮጵያ ክልል፤ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዞኖች፤ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልል ዞኖች፣ በሁሉም የሶማሌ ክልል ዞኖች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ ይጠበቃል። የጋምቤላ ክልል ዞኖች፣ የደቡብ ጎንደር፣ የሰሜን ወሎ እና ምሥራቅ ጎጃም ዞኖች፣ በትግራይ፣ ሐረሪ እና ድሬዳዋ በአንዳንድ ሥፍራዎቻቸው ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ኢንስቲትዩቱ ጠቁሟል። በአንዳንድ የሀገሪቱ ክፍሎች የሚኖረው እርጥበት ዘግይተው ለተዘሩና የእድገት ጊዜያቸውን ላልጨረሱ የመኸር ሰብሎች ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር መሆኑንም አመላክቷል። ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት እና ጥምር ግብርና ለሚያካሂዱ ለደቡባዊው የሀገሪቱ ክፍሎች ቀደም ብሎ የማሳ ዝግጅት ለማድረግና ዘር ለመዝራት ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥርም ጠቁሟል፡፡ እርጥበቱ ለአርብቶ አደሩና ከፊል አርብቶ አደር አካባቢዎች ለአረንጓዴ እፅዋት ልምላሜ መሻሻልና የውሃ አቅርቦት አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረውም ተጠቁሟል። ውሃ አጠር የሆኑ አካባቢዎች የሚገኘውን የዝናብ ውሃ ለመሰብሰብና ለማከማቸት መልካም አጋጣሚ ስለሚያገኙ ይህንኑ ለማከናወን የሚያስችል ዝግጅት እንዲያደርጉም በመግለጫው ተመላክቷል። በሌላም በኩል በአንዳንድ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚኖረው ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብ በደረሱ ሰብሎች ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ሊያሳድር እንደሚችልም ተገምቷል። በመሆኑም ከወዲሁ የደረሱ ሰብሎችን በወቅቱ በማንሳት አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲደረግ ሲል ኢንስቲትዩቱ አስገንዝቧል።
ተቋማት የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ በአግባቡ እንዲያስወግዱ የሚያስችል አሠራር ለመዘርጋት እየተሰራ ነው - አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን
Oct 4, 2023 334
አዲስ አበባ፣ መስከረም 23/2016(ኢዜአ)፦ የመንግሥትና የግል ተቋማት የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ በአግባቡ እንዲያስወግዱ የሚያስችል አሠራር ለመዘርጋት እየሰራ መሆኑን አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ገለጸ። በኢትዮጵያ የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ ክምችት እየጨመረ መምጣቱን መረጃዎች ያሳያሉ። ለአብነትም ከሦስት ዓመታት በፊት የተካሄደ ጥናትም በኢትዮጵያ 43 ሺህ ቶን የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ ክምችት መኖሩን አመላክቷል። በአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የአካባቢ ሕግ ተከባሪነት ዳይሬክተር ጄኔራል ግርማ ገመቹ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ባለፉት ሦስት ዓመታት ከኤሌክትሪክና ከቴክኖሎጂ መስፋፋት ጋር ተያይዞ የቆሻሻ ክምችቱ እየጨመረ መምጣቱን ተናግረዋል። በተለይም የመንግሥት ተቋማት የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻን በማከማቸት በኩል ተቀዳሚ ተጠቃሽ መሆናቸውንም በመጠቆም። በመንግሥት ግዥ አገልግሎት የንብረት ማስወገድ መሪ ሥራ አስፈጻሚ ሹንቃ አዱኛ፤ በተመሳሳይ የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻን ክምችት ጨምሯል ብለዋል። ለዚህም የመንግሥት ተቋማት የማይጠቀሙባቸው የኤሌክትሮኒክስና ኤሌክትሪክ ዕቃዎችን እንዲወገዱ የሚያወጡት የጨረታ መነሻ ዋጋ ከፍተኛ መሆን በምክንያትነት አንስተዋል። እነዚህን የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ ክምችት በአካባቢ ላይ የሚያደርሱትን አሉታዊ ተጽዕኖ ከግምት በማስገባት ተቋማት በአግባቡ እንዲያስወግዱ ጥሪ አቅርበዋል። የመንግሥትና የግል ተቋማት የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ መሳሪያ በድጋሚ መጠቀምን፣ ማደስንና መልሶ ጥቅም ላይ የማዋልን ዝንባሌያቸውን ማጠናከር አለባቸው ብለዋል። ባለሥልጣኑ በተያዘው ዓመት ከውጭ የሚገቡ ዕቃዎች አገልግሎታቸውን ሲጨርሱ ለአምራቹ እንዲመለሱ ማድረግ የሚያስችለውን የተራዘመ የአምራችነት ሥርዓት ምዝገባን ተግባራዊ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል። ይህም አስመጪዎች ከአምራቾች ጋር ጠንካራ ግንኙነት እንዲፈጥሩና የሚያስመጡትም ዕቃ ጥራት ያለው እንዲሆን ከማገዝ ባለፈ የቆሻሻ አስተዳደሩ ሥርዓቱን የተሳለጠ ያደርጋል ነው ያሉት። እንደ አቶ ሹንቃ ገለጻ፣ ቀደም ሲል የመንግሥት ተቋማት የማይገለገሉባቸውን የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ዕቃዎች ወደ ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በማምጣት ሲያስወግዱ መቆየታቸውን አስታውሰዋል። ይሁንና ከ2015 ዓ.ም ጀምሮ ይህ አሠራር ቀርቶ ተቋማት በራሳቸው ንብረቶቹን እንዲያስወግዱ መመሪያ መሰጠቱን ገልፀዋል። ይሁንና ተቋማቱ የማይገለገሉባቸውን የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ዕቃዎች እንዲያሳውቁ በማድረግ ንብረቶቹ በፍጥነትና በአግባቡ የሚወገዱበት መንገድ ለማመቻቸት ተቋማቸው እየሰራ መሆኑንም ጠቅሰዋል። የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ደንብ 425/2011 ላይ በግልፅ እንደተመላከተው የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ፣ ከጨረር አመንጪ መሳሪያዎች ውጭ ሁሉም ዓይነት የተጣለ የኤሌክትሪክና የኤሌክትሮኒክ መሳሪያ እና የመሳሪያ ክፍል የሚያጠቃልል ነው።
በአገሪቷ የተለያዩ አካባቢዎች ዝናብ ሰጪ የሜቲዎሮሎጂ ገጽታ በተጠናከረ መልኩ ይቀጥላል- ኢንስቲትዩቱ
Oct 3, 2023 333
አዲስ አበባ፤ መስከረም 22/2016 (ኢዜአ)፦ በአገሪቷ የተለያዩ አካባቢዎች ዝናብ ሰጪ የሜቲዎሮሎጂ ገጽታ በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ከመስከረም 20 እስከ ጥቅምት 20 ቀን 2016 ዓ.ም የሚኖረውን የአየር ሁኔታ በማስመልከት ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ መግለጫ ልኳል። በመግለጫውም በአገሪቷ የተለያዩ አካባቢዎች ዝናብ ሰጪ የሜቲዎሮሎጂ ገጽታ በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አስታውቋል። በምዕራብና በደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች የዝናብ ሰጪ የሜቲዎሮሎጂ ገጽታ የተሻለ ይሆናል ብሏል። የአየር ሁኔታው በሂደት ወደ ደቡብ የሀገሪቱ ክፍሎች ላይ የተሻለ እርጥበት እንደሚኖረው አስታውቋል። በመሆኑም ወቅታዊ ዝናብ ማግኝት በሚጀምሩና ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው ለሆኑት የደቡባዊ የሀገሪቱ ክፍሎች ቀደም ብሎ የማሳ ዝግጅት ለማድረግና ዘር ለመዝራት ምቹ መሆኑን አመላክቷል። እርጥበታማው የአየር ሁኔታ ወደ ደቡብና ደቡብ ምስራቅ አካባቢዎች የሚያደርግው መስፋፋት በአካባቢው ለሚኖሩ አርብቶ አደሮችና ከፊል አርብቶ አደሮች ለግጦሽ ሳርና ለመጠጥ ውሃ አቅርቦት ጥሩ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ተብሏል። በተመሳሳይ በምዕራብ እና በደቡብ ምዕራብ አካባቢዎች የዝናቡ ሁኔታ ቀጣይነት የሚኖረው በመሆኑ ቀደም ብለው ለተዘሩና አልፎ አልፎ ፍሬ በመሙላት ላይ ለሚገኙ ሰብሎችም እርጥበታቸውን ጠብቀው ላመቆየት እንደሚረዳ ተመላክቷል። በተጨማሪም ዘግይተው ለተዘሩና በተለያየ የእድገት ደረጃ ላይ ለሚገኙ የመኸር ሰብሎች የውሃ ፍላጎትን ለማሟላት ጠቃሚ መሆኑን ጠቁሟል።