ቀጥታ፡
አካባቢ ጥበቃ
የኢትዮጵያ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤን ለማስተናገድ መመረጥ የታዳሽ ኃይል ልማት ቁርጠኝነቷን የሚያረጋግጥ ነው
Nov 28, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ህዳር 19/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት(COP-32) ጉባኤ ለማስተናገድ መመረጥ ለታዳሽ ኃይል ልማት ትግበራ ቁርጠኝነቷን የሚያረጋግጥ መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሃብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር) ገለጹ። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሃብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር)፤ ኢትዮጵያ በሁሉም የታዳሽ ኃይል አማራጭ ዕምቅ የመልማት አቅም አላት። በኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ግንባታም የውሃ፣ የፀሐይ፣ የነፋስ፣ ጂኦተርማልና መሰል የኃይል አማራጮች ወሳኝ ሚና እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል። በገጠር አካባቢ የሚኖሩ ዜጎችን በፀሐይ ኃይል የኤሌክትሪክ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ እንደሚገኝም ተናግረዋል። የኤሌክትሪክ ኃይል ባልተዳረሰባቸው የገጠር መንደሮችና ከተሞች የፀሐይ ኃይል ተጠቃሚነት ለማሳደግ ከልማት አጋሮች ጋር በትብብር እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል ልማት ስኬትም የካርቦን ልቀትና የአየር ንብረት ለውጥ ስጋትን በመቀነስ ዓለም አቀፍ እውቅና እያስቸራት መሆኑን አብራርተዋል።   የበለጸጉ ሀገራት ዕድገታቸውን ለማረጋገጥ የተጓዙበት መንገድ በካይ ጋዞችን በመጠቀም በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ዓለምን ዋጋ እያስከፈሉ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በኢትዮጵያ የሚገነቡ የታዳሽ ኃይል አማራጭ መሠረተ ልማቶችም በአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ እየተፈተነ ለሚገኘው ዓለም ከፍተኛ ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን ጠቅሰዋል። የታዳሽ ኃይል መሠረተ ልማት ግንባታም የኢትዮጵያን ዓለም አቀፍ የኢንቨስትመንት ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ወሳኝ ሚና እየተወጣ እንደሚገኝ አብራርተዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ኃይል አማራጭ ልማት ቀጣናዊ የኃይል ትስስርን በማጠናከር ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ጉባኤዎችን የምታስተናግድበትን ዕድል መፍጠሩን አስረድተዋል። በብራዚል በተካሄደው መድረክ ኢትዮጵያ ኮፕ-32 ጉባኤን ለማስተናገድ ስትመረጥ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት ያስመዘገበችው ስኬት ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ኮፕ-32 ጉባኤን ለማስተናገድ መመረጧ በታዳሽ ኃይል አማራጭ፣ አረንጓዴ ዐሻራ እና በታዳሽ ኃይል ልማት ላስመዘገበችው ስኬት ዕውቅና የሚሰጥ መሆኑንም ሚኒስትሩ ተናግረዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርም የኢትዮጵያ የውሃ ሃብቶችን ደኅንነት በመጠበቅና የኃይል ማመንጫ ግድቦችን ከደለል በመታደግ ወሳኝ ድርሻ እየተጫወተ ነው ብለዋል። በብራዚል ቤለም በተካሄደው 30ኛ ጉባኤ ላይ ከሁለት ዓመታት በኋላ የሚካሄደውን 32ኛ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤ (COP-32) ኢትዮጵያ እንድታስተናግድ መመረጧ ይታወቃል።
በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለተተከሉ ችግኞች በተደረገ እንክብካቤ የጽድቀት መጠንን ማሳደግ ተችሏል
Nov 28, 2025 49
ደብረ ማርቆስ ፤ ሕዳር 19/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን ባለፈው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ለተተከለው ችግኝ የእንክብካቤ ስራ እየተካሄደ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የተፈጥሮ ሃብት ቡድን መሪ አቶ ንጉሴ ሽመልስ ለኢዜአ እንደገለጹት የሚተከሉ ችግኞችን የጽድቀት መጠን በመጨመር የደን ሽፋኑን ለማሳደግ የእንክብካቤ ስራ እየተሰራ ነው።   በዚህም ባሳለፍነው ክረምት ከተተከለው ከ219 ሚሊዮን በላይ ችግኝ ውስጥ 87 በመቶ የሚሆነው መጽደቅ መቻሉን ገልጸዋል። በዚህ ዓመት የተመዘገበው የችግኝ ጽድቀት መጠን ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር ከሰባት በመቶ በላይ ብልጫ እንዳለው ተመልክቷል። ከ500 ሺህ በላይ የማህበረሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ ችግኞችን በማረም፣ በመኮትኮት፣ ውሃ በማጠጣትና ከእንስሳት ንክኪ ነጻ በማድረግ በተሰራው ስራ የጽድቀት መጠኑ እንዲጨምር ማስቻሉን ተናግረዋል። በዞኑ የአነደድ ወረዳ የጉዳለማ ቀበሌ ነዋሪ አቶ መንግስቱ ስሜነህ እንዳሉት፤ በአረንጓዴ ልማቱ የተተከሉ ችግኞች የመሬታቸውን ለምነት በመጨመር ምርታማነታቸው እንዲያድግ እያደረገ ነው። ይሄን በመገንዘብም ዘንድሮ የተተከሉ ችግኞች እንዲጸድቁ ለማድረግ በመጠበቅና በመንከባከብ የድርሻቸውን እየተወጡ መሆናቸውን ተናግረዋል።   የደጀን ወረዳ የሽንቡሪ ቀበሌ ነዋሪ አቶ አንዷለም አምሳሉ በበኩላቸው ፤ በየዓመቱ የሚተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ የጽድቀት መጠኑ እንዲጨምር እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የተተከሉ ችግኞች የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ ማድረጋቸውን ጠቁመው በቀጣይም ችግኞችን የመትከልና የመንከባከብ ስራን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ የተሰሩ ተግባራት የዞኑን የደን ሽፋን ባለፈው ዓመት ከነበረበት ከ17 ነጥብ 4 በመቶ ወደ 18 ነጥብ 1 በመቶ ማሳደግ መቻሉን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤን እንድታዘጋጅ መመረጧ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ለሰራቻቸው ውጤታማ ሥራዎች የተሰጠ ዓለም አቀፍ ዕውቅና ነው 
Nov 27, 2025 121
አዲስ አበባ፤ሕዳር 18/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የኮፕ-32 ጉባኤን እንድታዘጋጅ መመረጧ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ለሰራቻቸው ውጤታማ ሥራዎች ዳግም የተሰጠ ዓለም አቀፍ ዕውቅና መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው ዋና ዋና የዲፕሎማሲ ስራዎችን አስመልክተው ለመገናኛ ብዙሀን መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም ኢትዮጵያ ጉባኤውን እንድታዘጋጅ መመረጧ በአረንጓዴ ልማት፣ በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ማበረታቻ፣ በአረንጓዴ ዐሻራ እና መሰል የአየር ንብረት ጥበቃ ሥራዎች ላይ እያከናወነች ለሚገኙ ተግባራት የተሰጠ እውቅና ነው። ኢትዮጵያ የኮፕ-32 አስተናጋጅ ሆና መመረጧ በዲፕሎማሲው መድረክ ያላት ተሰሚነት ወደ ላቀ ደረጃ እየተሸጋገረ ለመምጣቱ ትልቅ ማሳያ መሆኑንም ጠቁመዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዮስ (ዶ/ር) የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ (ኮፕ-32) ተወካይ ፕሬዝዳንት ሆነው መመረጣቸውንም ተናግረዋል። ጉባኤው ኢትዮጵያ አጀንዳዎቿን ለዓለም የምታስተዋውቅበት ትልቅ መድረክ እንደሚሆንም አምባሳደሩ ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው የቡድን-20 ጉባኤ ላይ በመሳተፍ የዲፕሎማሲ ስኬት ማስመዝገቧን ጠቅሰዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጉባኤው ባደረጉት ንግግር የአፍሪካን ሁነኛ አጀንዳዎችን ማንጸባረቃቸውንም አስታውሰዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከተመድ፣ ከዓለም ባንክ፣ ከአፍሪካ ልማት ባንክ፣ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (IMF) እና ከተለያዩ ሀገራት መሪዎች ጋር ውጤታማ የጎንዮሽ ውይይቶችን ማድረጋቸውንና በርካታ ስምምነቶች መፈጸማቸውን ገልጸዋል። የማሌዥያና የሲንጋፖር ሀገራት መሪዎች የሥራ ጉብኝት ኢትዮጵያ ካላት ሁለገብ የልማት ጉዞ አንፃር ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ከሀገራቱ ጋር በነዳጅ፣ በታዳሽ ኃይል፣ በግብርና፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በስማርት ከተማ ልማት እና በሌሎችም ጉዳዮች ላይ ስምምነት መደረጉን አስታውቀዋል። በተሰሩ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ሥራዎች ምክንያት የተለያዩ ሀገራት ኤምባሲያቸውን በአዲስ አበባ የከፈቱ ሲሆን፣ ሌሎችም ለመክፈት መወሰናቸው በመግለጫው ተመላክቷል። በዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ መስክ የተከናወኑ ተግባራትን በተመለከተም፤ በሳውዲ አረቢያ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ ወደ 23 ሺህ የሚጠጉ ዜጎችን በቅርቡ ወደ ሀገር መመለስ እንደተቻለ ተመላክቷል። ኢትዮጵያ በብራዚል ቤለም በተካሄደው የዓለም የአየር ንብረት (COP-30) ጉባኤ ላይ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት (COP-32) ጉባኤ ለማስተናገድ መመረጧ ይታወቃል።  
መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉና ለዱር እንስሳት ሀብት የሰጠው ትኩረት ለዱር እንስሳት ጥበቃ ምቹ መደላድል ፈጥሯል
Nov 27, 2025 110
አዲስ አበባ፤ህዳር 18/2018(ኢዜአ)፦መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉና ለዱር እንስሳት ሀብት የሰጠው ትኩረት ለዱር እንስሳት ጥበቃና ባለስልጣኑ ለሚያከናውነው ተግባር ምቹ መደላድል መፍጠሩን የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ ገለፁ። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ በትናንትናው እለት በለንደን በተካሄደው በአፍሪካ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ የሚሰጠው ፕሪንስ ዊሊያም አዋርድ የ2025 አሸናፊ ሆነዋል። ዋና ዳይሬክተሩ አሸናፊ የሆኑት ተስክ ጥበቃ ሽልማት 2025 በተዘጋጀው በአፍሪካ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ የላቀ ድርሻና አስተዋፅኦ ላበረከቱ ሰዎች በሚሰጠው የህይወት ዘመን አበርክቶ ሽልማት ዘርፍ ነው። አቶ ኩመራ በዱር እንስሳት ጥበቃ ዘርፍ ከባለሙያነት እስከ ዋና ዳይሬክተርነት ከ30 ዓመት በላይ ያገለገሉ ሲሆን በዘርፉ በተለያዩ የጥናት እና ምርምር እንዲሁም የአስተዳደር ሥራዎች ላይ ያበረከቱት የላቀ አስተዋጽኦ ሽልማቱን ለማሸነፍ አስችሏቸዋል። የኢትዮጵያ የዱር እንስሳት ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ኩመራ ዋቅጅራ እንዳሉት ባለስልጣኑ የዱር እንስሳትና መኖሪያ አካባቢያቸው በአግባቡ ተጠብቆና ለምቶ በዘላቂነት ጥቅም ላይ ለማዋል እየሰራ ይገኛል። የጥበቃ ቦታዎችን በጥናት ለይቶ በህብረተሰቡ ተሳትፎ ማቋቋም እንዲሁም የአስተዳደር ስርዓት ዘርግቶ በአግባቡ እንዲጠበቁና እንዲለሙ የማድረግ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። ባለስልጣኑ የዱር እንስሳት መጠለያ፣ የስፖርታዊ አደን የሚካሄድባቸው ጥበቃ ቦታዎችን ጨምሮ በተለያዩ ምድብ ያሉ የጥበቃ ቦታዎች በአግባቡ እንዲጠበቁ የማድረግ ስራም ያከናውናል ነው ያሉት። የጥበቃ ስራዎችን ከክልሎች፣ከማህበረሰቡ የሚመለከታቸው አካላት ጋር ከመስራት ባለፈ በዱር እንስሳት ላይ የሚፈፀሙ ወንጀሎችን ለመከላከል ከአገራት ጋር በመተባበር እንደሚሰራም ተናግረዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መንግስት ለቱሪዝም ዘርፉና ለዱር እንስሳት ሀብት የሰጠው ትኩረት ለዱር እንስሳት ጥበቃና ባለስልጣኑ ለሚያከናውነው ተግባር ምቹ መደላድል መፍጠሩን ጠቁመዋል። ያገኙት ሽልማትም ዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አለም አቀፍ እይታ እንዲያገኝ ለማስቻሉ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። ሽልማቱ ለዱር እንስሳት ጥበቃ የበለጠ ድምፅ ለመሆን፣ ህፃናት ለተፈጥሮ ሀብት ያላቸውን ተቆርቋሪነት ለማሳደግና የተፈጥሮ ሀብት አርበኛ የሆኑት ሬንጀሮች ማህበር የበለጠ ለማጠናከር እንዲተጉ የቤት ስራ የሚሰጥ ነው ብለዋል።
ፓርኩ በተደረገለት ጥበቃና እንክብካቤ የዱር እንስሳት ቁጥር እየጨመረ ነው 
Nov 26, 2025 180
ገንዳውኃ፣ ሕዳር 17/2018(ኢዜአ)፡ - የጎደቤ ብሔራዊ ፓርክ በተደረገለት የብዝኃ ህይወት ጥበቃና እንክብካቤ የዱር እንስሳቱ ቁጥር እየጨመረ እፅዋቱም እየተስፋፉ መሆኑን የፓርኩ ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ይርጋ ታከለ፤ የፓርኩን ደህንነት ለመጠበቅ በመንግስት እየተደረገ ያለውን ጥረት እንዲያግዙ ከሃይማኖት አባቶችና ከሌሎችም የአካባቢው የሕብረተሰብ ክፍሎች ጋር ተደጋጋሚ ውይይትና ምክክር መደረጉን ለኢዜአ ገልጸዋል። በዚህም ሕብረተሰቡ ገንዘብና ቁሳቁስ በማዋጣት ጭምር በፓርኩ ውስጥ የስካውት መጠለያ ካምፕና የንፁህ መጠጥ ውሃ ግንባታ በማከናወን የተጠናከረ ጥበቃ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ተከትሎም በፓርኩ ውሰጥ የሚገኘው የአጥቢ እንስሳት ዝርያ ቁጥር ከ27 ወደ 30 ሲያድግ እፅዋቶች ደግሞ እየተስፋፋ መምጣታቸውን አስረድተዋል።   በተጨማሪም በሕገወጥ አደንና ደን ጭፍጨፋ ተሰደው የነበሩ የዱር እንስሳት እንዲመለሱና በመጥፋት ላይ የነበሩ የእፅዋት ዝርያዎች እንደገና እንዲያገግሙ ማስቻሉንም አንስተዋል። ፓርኩ በአብዛኛው የሳር እና ቁጥቋጦ ዝርያ የበዛበት ቢሆንም ትላልቅ የደን ዛፎች ባለቤት እንደሆነም በጥናት መለየቱን አስታውቀዋል። በፓርኩ ከእንስሳት የቆላ አጋዘን፣ ነብር፣ ጅብ፣ ጉሬዛ ያሉ ሲሆን፤ ከአእዋፋት ደግሞ ባለነጭ ጀርባ የአፍሪካ ጆፌ አሞራ፣ ቆቅ፣ ዥግራና ሌሎች የዱር እንስሳት፤ እንዲሁም ከደን እፅዋት " ዞቢ ፣ ዲዛ ፣ ኩመር ፣ ወይባ፣ አባሎ፣ ሰርኪን " እና ሌሎችም በፓርኩ ውስጥ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል።   ይሄን የሀገር ትልቅ ሃብት በሰፊው በማስተዋወቅና ጎብኚዎች ወደ አካባቢው እንዲመጡ በማድረግ ከዘርፉ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግና የአካባቢውን ሕብረተሰብ ተጠቃሚ ለመድረግ ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል። ከአካባቢው ነዋሪዎች መካከል አቶ አምሳሉ ደረጀ በሰጡት አስተያየት፤ ከዚህ በፊት በፓርኩ ክልል ውስጥ የቤት እንስሳት ስምሪት፤ ደን ጭፍጨፋና ሕገወጥ አደን በብዛት ይካሄድ እንደነበር አውስተዋል።   አሁን ፓርኩን መጠበቅ የጽሕፈት ቤቱ ብቻ ሳይሆን የሁሉም ማህበረሰብ ኃላፊነት መሆኑን ተገንዝበው ድጋፍ በማድረግ ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን ገልጸዋል። ፓርኩ የሀገር ሀብት ነው፤ ይህን ሀብት በመጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድ ማስተላለፍ ደግሞ የእኛ ሃላፊነት ነው ያሉት ደግሞ አርሶ አደር ደመቀ ሰማ ናቸው። በፓርኩ ላይ ጉዳት የሚያስከትሉ ግለሰቦች ተይዘው እንዲቀጡ በማድረግ ለፓርኩ ደሕንነት መጠበቅ የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ተናግረዋል።   በምዕራብ ጎንደር ዞን ምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ እና በመተማ ወረዳ መካከል የሚገኘው የጎደቤ ብሄራዊ ፓርክ በጥብቅ ደንነት ከቆየ በኋላ በአማራ ክልል ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 152/2009 ዓ.ም ፓርክ ሆኖ የተቋቋመና 18ሺህ 691 ሄክታር ስፋት ያለው መሆኑ ተጠቁሟል። ፓርኩ ከባሕርዳር በ411 ኪሎ ሜትር፣ ከጎንደር ደግሞ በ237ኪሎ ሜትር እንዲሁም ከዞኑ ማዕከል ገንዳውሃ ከተማ ደግሞ በ133 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ እንደሚገኝ ተመልክቷል።
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) የኮፕ 32 ተወካይ ፕሬዝደንት በመሆን ተመደቡ
Nov 26, 2025 114
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 17/2018(ኢዜአ)፦ መንግስት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)ን የኮፕ 32 ተወካይ ፕሬዝደንት አድርጎ መድቧል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጸህፈት ቤት እንዳስታወቀው፤ በተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ማእቀፍ ኮንቬንሽን መሠረት ኢትዮጵያ የኮፕ 32 አስተናጋጅ ሀገር መሆኗን ተከትሎ የኢትዮጵያ መንግሥት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሆኑትን ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)ን የኮፕ 32 ተወካይ ፕሬዝደንት አድርጎ መድቧል። ዶክተር ጌዲዮን ከሀገር ውስጥ የሥራ ኃላፊዎች፣ ከተባበሩት መንግሥታት አካላት እና አለም አቀፍ አጋሮች ጋር በመተባበር የኮፕ 32 ዝግጅትን እንደሚመሩም አስታውቋል። የኢትዮጵያ መንግሥት የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ማእቀፍ ኮንቬንሽን አባል ሀገራት ለኢትዮጵያ የማዘጋጀት ኃላፊነት በመስጠታቸው ምስጋናውን አቅርቧል፡፡ በዶክተር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ አስተባባሪነት ከአለም የአየር ንብረት ጥበቃ ማኅበረሰብ ጋር በቅርበት ለመሥራት ዝግጁ መሆኑንም ገልጿል፡፡
ዝቅተኛ በካይ ጋዝ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ርብርብ እየተደረገ ነው
Nov 24, 2025 260
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 15/2018 (ኢዜአ)፡- በትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ዘርፍ ዝቅተኛ በካይ ጋዝ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። ሚኒስቴሩ ከፓወር አፍሪካ ጋር በመተባበር የሚያዘጋጀው ሁለተኛው ኢትዮ ግሪን ሞቢሊቲ 2025 ኤግዚቢሽንና ባዛር ከታኅሣሥ 9 እስከ 12 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ያካሂዳል፡፡ ሚኒስትሩ አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ሁለተኛውን ኢትዮ ግሪን ሞቢሊቲ 2025 ኤግዚቢሽንና ባዛር ለማካሄድ በተደረጉ ዝግጅቶችና በሚጠበቁ ውጤቶች ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል።   ሚኒስትር አለሙ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት መተግበር የጀመረው አረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ መደላድል እየፈጠረ ነው። የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ ሥራዎች ኢትዮጵያ ኮፕ 32 የዓለም አየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ እንድታስተናግድ እንድትመረጥ አድርጓታል ሲሉም ጠቅሰዋል። በትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ዘርፍም ታዳሽ ኃይልም ሆነ ዝቅተኛ በካይ ጋዝ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎች በስፋት ጥቅም ላይ ለማዋል ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። ከታኅሣሥ 9 እስከ 12 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ የሚካሄደው ኢትዮ ግሪን ሞቢሊቲ ኤግዚብሽንና ባዛር ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ አዎንታዊ ሚና እንደሚጫወትም ተናግረዋል።   በኤግዚቢሽን እና ባዛሩ ላይ ኤሌክትሪክን ጨምሮ የተለያዩ ታዳሽ ኃይል የሚጠቀሙ ተሽከርካሪ አምራቾች፣ ቴክኖሎጂ አቅራቢዎች፣ በዘርፉ የተሰማሩ ዓለም አቀፍ ተቋማት እና የጥናትና ምርምር ተቋማት እንደሚሳተፉ አብራርተዋል። በዘርፉ የሚስተዋሉ ችግሮችና መፍትሔ አቅጣጫዎች ላይ በጋራ ውይይት የሚደረግበት መርሐ ግብር መሰናዳቱንም አመልክተዋል።
በገጠር ክላስተሮች እየተከናወነ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ ነው
Nov 22, 2025 260
ድሬዳዋ፤ ሕዳር 13/2018(ኢዜአ) ፡- በድሬዳዋ የገጠር ክላስተሮች እየተከናወነ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ለስነ ምህዳር ጥበቃና ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ መሆኑን የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ባለሙያ አቶ ገረመው ረጋሳ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ በድሬዳዋ የገጠር ክላስተሮች የአፈርና የውሃ ጥበቃ ስራ በስፋት በመከናወን ላይ መሆኑንና በዚህም ውጤት እየመጣ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   በድሬዳዋ የገጠር ክላስተሮች እየተከናወነ ያለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ለስነ ምህዳር ጥበቃና ምርታማነትን ለማሳደግ እያገዘ ስለመሆኑ አንስተዋል። በዘመቻ እና በመደበኛ መርሃ ግብር በተራቆቱ ተፋሰሶች ላይ በተከናወኑ የልማት ስራዎች ከ60 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ማልማት መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመጠበቅም ባለፈ ምርታማነትን ማሳደግ ማስቻሉን ገልጸዋል። በቢሮው የህብረት ስራ ማስፋፊያ፣ ግብይትና ግብአት ኤጀንሲ ባለሙያ አቶ ያሲን ኢብራሂም፤ የተፋሰስ ልማት ስራ የአካባቢ ስነ ምህዳርን በመጠበቅ ረገድ የሚታይ ውጤት የመጣበት መሆኑን ተናግረዋል።   በተለይም በገጠር አካባቢዎች ምርታማነትን በማሳደግ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ያስቻለ መሆኑንም አንስተዋል። በድሬዳዋ የገጠር ክላስተሮች ወጣቶችና ሴቶች ተደራጅተው በሌማት ትሩፋት ኢንሸቲቮች ላይ በመሳተፍ ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። የለገ ዶል ገጠር ቀበሌ አርሶ አደር ኢብሳ ሙሳ እና አርሶ አደር አህመድ ዳዌ፤ በአካባቢው የተከናወነው የልማት ስራ በብዙ መልኩ የጠቀማቸውና ውጤትም ያገኙበት መሆኑን ተናግረዋል።   የቀበሌው የግብርና ባለሙያ አቶ ምህረት መታዬት፤ አርሶ አደሮቹ በአትክልትና ፍራፍሬ እንዲሁም በእንስሳት እርባታ በመሰማራት ስኬታማ መሆናቸውን ተናግረዋል።  
ኢትዮጵያ የዓለም የአየር ንብረት ጉባኤን እንድታስተናግድ መመረጧ ሀገሪቷ ለአየር ንብረት ለውጥ ፖሊሲና ስትራቴጂ ትግበራ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር ያረጋገጠ ነው 
Nov 21, 2025 305
አዲስ አበባ፤ሕዳር 12/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት (COP-32) ጉባኤን እንድታስተናግድ መመረጧ ሀገሪቷ ለአየር ንብረት ለውጥ ፖሊሲና ስትራቴጂ ትግበራ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር ያረጋገጠ ነው ሲሉ የአረንጓዴ አሻራ ሀገራዊ መርሃ-ግብር የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ገለፁ። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬቶችም ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት ጉልህ ድርሻ እየተወጣ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአካባቢ ስነ-ምኅዳር ደኅንነት በማስጠበቅ ጉልህ ሚና እየተጫወተ ይገኛል። ኢትዮጵያ በብራዚል ቤለም በተካሄደው የዓለም የአየር ንብረት (COP-30) ጉባኤ ላይ 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት (COP-32) ጉባኤ ለማስተናገድ መመረጧ ይታወቃል። አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉትም፤ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እስካሁን ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን በመትከል ዓለም አቀፍ ዕውቅናን ያስገኘ አስደማሚ የልማት ስኬት ተመዝግቧል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬትም 32ኛውን የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (COP-32) ለማስተናገድ ተመራጭ እንድትሆን ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም ገልጸዋል። ጉባኤው ላይ የበርካታ ሀገራት መሪዎች፣ የዓለም አቀፍ ተቋማት የስራ ኃላፊዎች ምክክር በማድረግ ውሳኔ የሚያሳልፉበት መድረክ በመሆኑ ልምድና ተሞክሮን ለመጋራት ትልቅ ትርጉም እንደሚሰጠው ተናግረዋል። የአየር ንብረት ጉባኤን ለማስተናገድ ጥያቄ የሚያቀርቡ ሀገራት በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሥርዓት የሚያከናወኑት የመሠረተ ልማት ግንባታ ስራና ያስመዘገቡት ስኬት እንደሚታይ አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ ተከላና የአየር ንብረት ፖሊሲና ስትራቴጂ ትግበራ ያላት ቁርጠኝነት ጉባኤውን ለማስተናገድ ያቀረበችው ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ እንዲያገኝ ማድረጉን አንስተዋል። በኢትዮጵያ የተካሄደው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤና ሌሎች ዓለም አቀፍ መድረኮችን በብቃት የማስተናገድ ልምድና አቅም ለመመረጧ ሌላኛው ዐብይ ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። የፓሪሱን ስምምነት ለመተግበር በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ፖሊሲና ስትራቴጂዎች ታሳቢ ያደረጉ የኢትዮጵያ የልማት ተነሳሽነቶችም በዓለም አቀፍ ደረጃ በአርዓያነት የሚወሰዱ መሆናቸውን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬቶችም ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የራሱን ድርሻ እየተወጣ እንደሚገኝም ተናግረዋል። አረንጓዴ አሻራ የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በመጠበቅ፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥና የሥራ ዕድል ፈጠራን በመደገፍ ሂደት የኢኮኖሚ ዕድገትን በማስቀጠል ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑንም ገልጸዋል። ለአየር ንብረት ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታም በ2050 ከካርቦን ልቀት ነፃ የኢኮኖሚ ሥርዓት ለመገንባት የተያዘውን ግብ ዕውን ለማድረግ ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል።
የመዲናዋ የወንዝ ዳር ልማቶች የወንዞች ደህንነት እንዲጠበቅ ጉልህ ሚና እያበረከቱ ነው
Nov 20, 2025 295
አዲስ አበባ፤ ህዳር 11/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የተከናወኑት የወንዝ ዳር ልማቶች ከህዝብ መዝናኛነታቸው ባሻገር የወንዞች ደህንነት እንዲጠበቅ ጉልህ ሚና መጫወታቸውን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የመዲናዋ ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ በአዲስ አበባ የፍሳሽ ማስወገጃዎችን ከወንዞች ጋር በማገናኘት ሲፈጠሩ በቆዩ ችግሮች ወንዞች ለብክለት ተጋልጠው ቆይተዋል፡፡ ይህም ወንዞቹ ለሰዎች፣ ለእንስሳትና ለዕፅዋት ጤንነትና ደህንነት ጥቅም ከመስጠት ይልቅ ስጋት እንዲሆኑ አድርጓቸው ቆይቷል፡፡ ይህን ተከትሎ በከተማዋ የተጀመረው የኮሪደር ልማት አድማሱን በማስፋት ወደ ወንዝ ዳርቻ ልማት በመሸጋገሩ የወንዞችን ደህንነት ማስጠበቅ ተችሏል፡፡ የወንዝ ዳር ፕሮጀክት መተግበር ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ የስጋት ምንጭ የነበሩት ወንዞች የመዝናኛ ማዕከል ሆነዋል፡፡ ኢዜአ በወንዝ ዳር ልማቶች በለሙ ቦታዎች ሲዝናኑ ያገኛቸው የተለያዩ ህብረተሰብ ክፍሎች እንደገለጹት ቦታዎቹ አማራጭ የእረፍት ማሳለፊያ ከመሆናቸው ባሻገር የከተማዋን ገጽታ ውብ አድርገውታል፡፡ አቶ መርሳ በቀለ በወንዞች ዳርቻ የተሰሩ የልማት ስራዎች ከዚህ ቀደም ለማየትም ሆነ በአካባቢው ለማለፍ አስቸጋሪ የነበሩ ቦታዎችን ውብና ጽዱ ያደረጉ ናቸው ብለዋል፡፡ ፕሮጀክቶቹ ወንዞችን ከብክለት ነፃ በማድረግ ደህንነታቸው ተጠብቆ ለህዝብ መዝናኛነት እንዲውሉ ከማስቻል ባለፈ አዲስ አበባን እንደ ስሟ ውብና ጽዱ እንዳደረጓት ገልጸዋል፡፡ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ግርማዬ ፍስሃ በበኩላቸው፤ የከተማዋ ወንዞች የቆሻሻ መጣያ እንደነበሩ አስታውሰው፤ በዚህ ደረጃ ለምተው በመመልከታቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል፡፡ የልማት ስራው ወንዞቹንና በዙሪያቸው ያሉ አካባቢዎችን ውብና ፅዱ ከማድረግ ባሻገር ኢትዮጵያዊያን በአካባቢ ጥበቃ ያላቸውን ልምድና ክህሎት ያሳዩበት መሆኑን የተናገሩት ደግሞ አቶ ጋዲሳ ዋቅጅራናቸው፡፡ በኮሪደር ልማትና በወንዝ ዳር ፕሮጀክቶች ለህፃናትና ወጣቶች የሚያገለግሉ ምቹ የሆኑ በርካታ መዝናኛዎች መገንባታቸውን የተናገሩት ወጣት ሰለሞን ዳዊት እና አብዲ መልካሙ ናቸው፡፡ መዝናኛ ቦታዎቹ ጊዜአችንን በአልባሌ ቦታ ከማሳለፍ ይልቅ በመልካም ድባብ በመታጀብ ንፁህ አየር እየወሰድን እንድንዝናና ዕድል ፈጥረውልናል ብለዋል፡፡ የልማት ስራዎቹ ከመዝናኛነት ባለፈ ህብረተሰቡ ስለ አካባቢ ጥበቃና እንክብካቤ ያለው ግንዛቤ እንዲጨምር የሚያስችሉ መሆናቸውን የገለጸው ወጣት ይታያል ደጋጋ ነው ፡፡
በክልሉ በክረምቱ ወራት ለተተከሉ ችግኞች በበጋው ወራት የሚደረገው እንክብካቤ ተጠናክሮ ቀጥሏል
Nov 20, 2025 218
ጋምቤላ፤ ህዳር 11/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከቡ ስራ በበጋው ወራትም ተጠናክሮ መቀጠሉን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ገለፀ። የጋምቤላ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አንድሪው ቱት ለኢዜአ እንደገለፁት በክረምቱ ወራት በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከቡ ስራ በበጋውም ወራት ተጠናክሮ ቀጥሏል። ህብረተሰቡ ችግኞችን ከመትከል ባለፈ የጽድቀት መጠናቸው እንዲጨምር እንክብካቤ እንዲያደርግ ግንዛቤ መፈጠሩን አንስተዋል። በአረንጓዴ ዐሻራ የለሙ አካባቢዎች ወደ ቀደመ ይዞታቸው እንዲመለሱ የእንክብካቤና የጥበቃ ስራው እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብሩ የለሙ አካባቢዎችን በመጠበቅ ለስራ እድል ፈጠራ እንዲውሉ በማህበር ለተደራጁ ወጣቶች መተላለፋቸውንም ተናግረዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ ልማቱ ከስራ ዕድል ፈጠራው ባለፈም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራን በማሳደግ የአርሶና አርብቶ አደሩን ምርታማነት በመጨመር የምግብ ዋስትናን እያረጋገጠ እንደሚገኝም ተናግረዋል። ለአብነትም ባለፉት ዓመታት የተተከሉት ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያላቸው የማንጎ፣ የፓፓያ፣ የሙዝና ሌሎች የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች የአርሶ አደሩን ህይወት መለወጥ መጀመራቸውን ገልፀዋል።   በክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና አጠቃቀም ዳይሬክተር ኬት ሉል በበኩላቸው በክልሉ በክረምቱ ወራት በአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መተከላቸውን ተናግረዋል፡፡ እነዚህን ችግኞች ከእንስሳትና ከሰው ንክኪ እንዲሁም ከሰደድ እሳት በመጠበቅና ለመንከባከብ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡ ለተግባራዊነቱ ስራ አጥ ዜጎችን በማደራጀት ችግኞችን በመንከባከብ ተግባር ላይ እንዲሰማሩ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ በክልሉ ባለፈው የክረምት ወራት በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞች የጽድቀት መጠንም 78 በመቶ መድረሱን አክለዋል፡፡
በአማራ ክልል የግሪሳ ወፍ በሰብል ላይ ጉዳት ሳያደርስ መቆጣጠር ተቻለ
Nov 19, 2025 226
ባሕርዳር/ ደሴ ፤ሕዳር 10/2018 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል ሶስት ዞኖች አንዳንድ አካባቢዎች የተከሰተው የግሪሳ ወፍ በሰብል ላይ ጉዳት ሳያደርስ መቆጣጠር መቻሉን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። ‎በቢሮው የዕፅዋት ጥበቃ ባለሙያ አቶ አበበ አናጋው ፤ የግሪሳ ወፍ በክልሉ ሰሜን ሸዋ፣ ደቡብ ወሎና ኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞኖች አንዳንድ አካባቢዎች መከሰቱን ለኢዜአ ተናግረዋል። ‎ቢሮው ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ከጥቅምት 8/2018 እስከ ሕዳር 6/2018 ዓ.ም ድረስ ባደረገው በአውሮፕላን የታገዘ የኬሚካል ርጭት በሰብል ላይ ጉዳት ሳያደርስ በቁጥጥር ስር ማዋል መቻሉን አስታውቀዋል።   ‎የኬሚካል ርጭቱ ‎ ግሪሳ ወፉ በሚያድርባቸው በተለዩ 604 ሄክታር የሚሸፍን ቦታዎች በተካሄደው ርጭት የግሪሳ ወፍ መንጋን ማስወገድ መቻሉን ገልጸዋል። ‎በርጭቱም 1 ሺህ 208 ሊትር ኬሚካል ጥቅም ላይ መዋሉን ጠቁመው፤ በዚህም ከ100 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የለማ ሰብልን ከጉዳት መታደግ መቻሉን ባለሙያው አስረድተዋል። በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ደጀኔ ከበደ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ጅሌ ጥሙጋ እና ደዋጨፋ ወረዳዎች የግሪሳ ወፍ መንጋ ተከስቶ ነበር። የወፉን ማደሪያ ሥፍራ በመለየት ከ155 ሄክታር መሬት ላይ በተደረገ የአውሮፕላን ኬሚካል ርጭት በሰብል ላይ ጉዳት ሳይደርስ መከላከል መቻሉን ተናግረዋል።   በደቡብ ወሎ ዞን ግብርና መምሪያ የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ይመር ሰይድ በበኩላቸው፤ በቃሉ ወረዳ የተከሰተውን የግሪሳ ወፍ በአውሮፕላን የታገዘ ኬሚካል ርጭት በቁጥጥር ስር ማዋል መቻሉን ተናግረዋል። አርሶ አደሩ የደረሰውን ሰብል በወቅቱ ፈጥኖ ከመሰብሰብ ባሻገር ተባይና የግሪሳ ወፍ ሲመለከት ፈጥኖ ለግብርና ባለሙያዎች መረጃ እንዲሰጥ መክረዋል።
አሳታፊ የደን አስተዳደር ስርዓት የተፈጥሮ ደኖችን ህልውና መጠበቅ አስችሏል
Nov 19, 2025 250
ሚዛን አማን፤ሕዳር 10/2018 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ተግባራዊ የተደረገው አሳታፊ የደን አስተዳደር ስርአት የተፈጥሮ ደኖችን ህልውና መጠበቅ ያስቻለ መሆኑን የክልሉ ደን፣ አካባቢ ጥበቃና የአየር ንብረት ለውጥ ቢሮ ገለጸ። በኢትዮጵያ ሰፊ የደን ሽፋን ካላቸው አካባቢዎች መካከል የሚጠቀሰው የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ሁለት በባዮስፌር ሪዘርቭ የተመዘገቡ ጥብቅ የተፈጥሮ ደኖች መገኛ ነው። የክልሉ ደን፣ አካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ለማ ገብረሚካኤል ለኢዜአ እንደገለጹት፤በክልሉ ከጥንት ጀምሮ ያለው የደን አጠባበቅ ባህል የደን ሃብቶችን መጠበቅ፣ ማልማትና መንከባከብ ያስቻለ እሴት ሆኖ ቀጥሏል።   በክልሉ ውስጥ ከሚገኘው አጠቃላይ የደን ይዞታ ውስጥ ከ760 ሺ ሔክታር በላይ የሚያካልሉ ሁለት ደኖች በባዮስፌር ጥብቅ የደን ስፍራነት በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት የተመዘገቡ መሆኑን ተናግረዋል። በካፋና ሸካ ዞኖች የሚገኙ ደኖችን ለመጠበቅ የተቋቋሙ ከ500 በላይ አሳታፊ የደን አስተዳደር ማኅበራት ለደኖቹ ሕልውና መጠበቅ የጎላ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን አንስተው በቀጣይም የደኖቹን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ለማሳደግና የኢኮቱሪዝም ቀጣና ለማድረግ የሚሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል። በሸካ ዞን የአንድራቻ ወረዳ ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሠራዊት ቆጭቶ በበኩላቸው፤ አሳታፊ የደን አስተዳደር ጥበቃ ሥርዓት ከሸካቾ ብሔረሰብ ባህል ጋር የተሳሰረ የሃብት መጠበቂያ እሴት መሆኑን ገልጸዋል።   በመሆኑም በሥርአቱ ደን ከመጠበቅ ባሻገር ከዘርፉ ኢኮኖሚ በማመንጨት አካባቢውን ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑበት መሆኑንም ተናግረዋል። በወረዳው የዮኪጭጪ ቀበሌ አሳታፊ ደን አስተዳደር ማህበር አባል አቶ ገብረሥላሴ ቶንዶሮ፤ ደንን መጠበቅ ከጥንት የወረስነው ባህል በመሆኑ የትኛውንም የደን ውጤት ያለ ፍቃድና ያለ አግባብ መቁረጥ አይቻልም ብለዋል።   ደኑ በደን ክልልነት ከተመዘገበ በኋላም በአሳታፊ ደን አስተዳደር ተደራጅተው ለደኑ ጥበቃ ከማድረግ ጎን ለጎን በውስጡ ማርን ጨምሮ ኮሮሪማ፣ ጥምዝና ሌሎች የደን ውጤቶችን በማምረት እየተጠቀሙ መሆኑን ተናግረዋል። የደን ሃብት ጥበቃ የቀደሙት ያወረሱን ሀብታችን በመሆኑ ጠብቆ ለትውልድ የማስተላለፍ ግዴታ አለብን ያለው ደግሞ የዩቲ ቀበሌ የአሳታፊ ደን አስተዳደር ማኅበር አባል ወጣት ተካልኝ ተሰማ ነው።   ተገቢ ባልሆነ መንገድ የሚቆረጥ ዛፍ እንዳይኖር በአሳታፊ የደን አስተዳደር በወጣው የጥበቃ መርሐ ግብር መሠረት ደኑን እየጠበቀ መሆኑን ገልጿል። የአሳታፊ ደን አስተዳደር ማኅበር የአንድ ቀበሌ ነዋሪና በደን አካባቢ ያሉ አባወራ የህብረተሰብ ክፍሎችን በአባልነት ያቀፈ ሲሆን በደን ክልል ውስጥ ሕገ ወጥ ድርጊት እንዳይፈጸም በጥበቃ የሚከላከሉበት ሥርአት ነው። አሳታፊ የደን አስተዳደር ስርአት ዓላማውም የደን ሀብትን ዘላቂነት ማረጋገጥ፣ የብዝሃ ሕይወትን መጠበቅ፣ የካርበን ክምችትን መጨመር እንዲሁም በአካባቢው የሚኖሩ ማህበረሰቦችን ኑሮ ማሻሻል እና ከደን የሚገኘውን ጥቅም ፍትሃዊ በሆነ መንገድ እንዲያገኙ ማድረግ ነው።
ባለፈው ክረምት በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞችን እየተንከባከብን ነው - አርሶ አደሮች
Nov 18, 2025 253
አምቦ፤ ህዳር 9/2018(ኢዜአ)፡- ባለፈው ክረምት በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተተከሉ ችግኞችን እየተንከባከቡ መሆኑን የምዕራብ ሸዋ ዞን አርሶ አደሮች ተናገሩ። አርሶ አደሮቹ ከዚህ ቀደም በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በተተከሉ ችግኞች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እያገኙ መሆናቸውን ጠቁመው ዘንድሮም በችግኝ እንክብካቤው ላይ አተኩረዋል።   ከጨሊያ ወረዳ አርሶ አደሮች መካከል አስፋው ድንቁ ባለፉት ዓመታት በተከናወነ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የተራቆተ እና የተጎዳ ማሳቸው አገግሞ አሁን ላይ በፊት ከሚያገኙት ምርት በእጥፍ እያገኙ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም የእርሻ ማሳቸው በጎርፍ ተጠርጎ ምርታማነቱ በመቀነሱ ስጋት ውስጥ ገብተው እንደነበረም አስታውሰዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከተጀመረ ወዲህ በተከታታይ በተተከሉ ችግኞች የአፈር መሸርሸር በመቀነሱ የእርሻ ማሳቸው ምርታማነቱ መጨመሩን አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅት የተለያዩ የጥራጥሬ ሰብሎችን እያለሙ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው የተተከሉ ችግኞች የመሬቱን ለምነት የሚጠብቁ በመሆኑ ለከብቶቻቸው መኖ ማግኘታቸውንና አካባቢያቸውም መልካም ገጽፅታ መላበሱን አውስተዋል።   ሌላው አርሶ አደር ፋይሳ ቀነኒ በበኩላቸው፣ በአካባቢያቸው የተጎዳ መሬት በአረንጓዴ ዐሻራ ልማት እንዲያገግም በመደረጉ ከዚህ ቀደም ከሚያለሙት የጥራጥሬ ሰብሎች በተጨማሪ ጥምር ጥቅም የሚሰጡ ችግኞችን በመትከል ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን አንስተዋል፡፡ መርሃ ግብሩ ከመጀመሩ በፊት ዝናብ ወቅቱን ጠብቆ ስለማይዘንብ ብዙ መቸገራቸውን አስታውሰው አሁን ላይ ግን ዝናቡም ወቅቱን ጠብቆ በመዝነቡ ምርታማነታቸው ጨምሮ የተሻለ ገቢ እያገኙ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ አርሶ አደሮቹ የአካባቢያቸውን ማህበረሰብ በማስተባበር የእርከን ስራ ላይ የአፈር ለምነት እንዲጠብቅና የተተከሉ ችግኞች እንዲጸድቁ ለተከታታይ ዓመታት በሰሩት ስራ ለውጥ መመዝገቡን ተናግረዋል።   የጨሊያ ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርናና መሬት አስተዳዳር ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኢነዑ ተሾመ በበኩላቸው፤ በወረዳው በሚከናወነው የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ስራ የህብረተሰቡ ተሳትፎ እያደገ መጥቷል ብለዋል፡፡ በወረዳው በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ለተተከሉት ችግኞች አስፈላጊው እንክብካቤ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በወረዳው የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ከተጀመረ ወዲህ የአካባቢው ስነ ምህዳር ከመቀየሩም በላይ የአርሶ አደሮቹ ምርትና ምርታማነት መጨመሩን አመልክተዋል። በወረዳው በአረንጓዴ ዐሻራ ልማት መርሃ ግብር ከሃገር በቀል የዛፍ ችግኞች በተጨማሪ ለምግብነት የሚውሉ ማንጐ፣ ሙዝ፣ አቮካዶ እና ቡና ጭምር መተከላቸውን ተናግረዋል፡፡
ሰውና ተፈጥሮ የተዋደዱበት ቆጠር ገድራ  ጥብቅ ደን
Nov 18, 2025 184
ሰውና ተፈጥሮ የተዋደዱበት ቆጠር ገድራ በጉራጌ ዞን ከሚገኙ የቱሪስት መዳረሻዎች መካከል አንዱ ነው። ጥብቅ ደኑ ከጉራጌ ዞን ከወልቂጤ ከተማ በ42 ኪሎ ሜትር ርቀት በስተምሥራቅ በእዣ ወረዳ ቆጠር ገድራ ቀበሌ ይገኛል።   ጥብቅ ደኑ በበርካታ ሀገር በቀል ዛፎች የተሸፈነ፣ ሰውና ተፈጥሮ የተዋደዱበት፣ ለአካባቢው ማህበረሰብ የህይወት እስትንፋስ ነው። የቆጠር ገድራ ጥብቅ ደን ቀልብን የሚስብ፣ ነፍስ በሀሴት የምትሞላበት፣ መንፈስ የሚታደስበት ውብ ስፍራ ነው። ቆጠር ገድራ ተዳፋታማ በሆነ ስፍራ የሚገኝ ሲሆን ብዛት ባላቸው ሀገር በቀል ዛፎች ማለትም ዝግባ፣ የኮሶ ዛፍ፣ የሀበሻ ፅድ የተሞላ ነው፡፡   የቆጠር ገድራ የተፈጥሮ ደን ለረጅም ዘመናት ከሰው ንክኪ ተጠብቆ የቆየው በአካባቢው ኅብረተሰብ ነባር ባህል መሠረት የጥንት አባቶች ደኑ እንዳይቆረጥ በቃል ኪዳን/ጉርዳ/ ስለተሳሰሩ መሆኑም ተገልጿል፡፡ 20ኛው የብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀንን ምክንያት በማድረግ ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተውጣጣ የጋዜጠኞች ቡድን በጉራጌ ዞን ከሚገኙ የቱሪዝም መዳረሻዎች አንዱ የሆነውን የቆጠር ገድራ ጥብቅ ደንን ጎብኝቷል።   የእዣ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ዘውዱ ዱላ በጉብኝቱ ወቅት እንደገለጹት ከጥንት ጀምሮ በአካባቢው ማህበረሰብ ዘንድ ደን መቁረጥ እንደ ወንጀል የሚቆጠር፤ በአካባቢው ባህል የሚያስቀጣ ነውር ተግባር ነው፡፡ ጥብቅ ደኑ ከ350 ሄክታር መሬት በላይ እንደሚሸፍን እና በውስጡ ከ18 በላይ የዛፍ ዝርያዎች እንደሚገኙም አንስተዋል። የዞኑ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ መሰረት አመርጋ በበኩላቸው የጉራጌ ህዝብ በስራ ወዳድነቱና ታታሪነቱ የሚታወቅ ከተፈጥሮ ጋር ትልቅ ቁርኝት ያለው መሆኑን ተናግረዋል። በጉራጌ ዞን እዣ ወረዳ የሚገኘው የቆጠር ገድራ ጥብቅ የተፈጥሮ ደን ከ700 ዓመታት በላይ እንዳስቆጠረ የሚነገርለት ሲሆን ህብረተሰቡ ደኑን ጠብቆ ያቆየበት መንገድ ከተፈጥሮ ጋር ላለው ቁርኝት አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል። ደኑን በዘላቂነት ጠብቆ በማቆየት አካባቢውን የቱሪስት መዳረሻ ለማድረግናና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሠራ መሆኑንም ተናግረዋል።   ቆጠር ገድራ ጥብቅ ደን በውስጡ ከያዛቸው የዛፍ ዝርያዎች ባለፈ የበርካታ ብዝኃ ህይወት መኖሪያ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የእዣ ወረዳ ደን እና አካባቢ ጥበቃ ልማት ጽህፈት ቤት የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ሂደት አስተባባሪ ብርሃኑ ብርሼ ናቸው። እንደዚህ ዓይነት ጥብቅ ደኖች ሥነ ምሕዳርን በመጠበቅ ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ተያይዘው የሚመጡ ችግሮችን ለመከላከል ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያበረክታሉ ብለዋል።
ኢትዮጵያ (ኮፕ 32)ን እንድታስተናግድ መመረጧ ለአየር ንብረት ለውጥ እርምጃ ላላት ጽኑ ቁርጠኝነት እውቅና የሰጠ ነው - ኢጋድ
Nov 15, 2025 185
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 32)ን እንድታስተናግድ መመረጧ ለአየር ንብረት ለውጥ እርምጃና አረንጓዴ ልማት ቁርጠኝነቷ እውቅና የሰጠ መሆኑን የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) ገለጸ። የድርጅቱ ዋና ጸሀፊ ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) ኢትዮጵያ ኮፕ 32 እንድታዘጋጅ መመረጧን ተከትሎ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ጉባኤውን ማዘጋጀቷ በአየር ንብረት እና ልማት ያላት መሪነት እያደገ መምጣቱን የሚያሳይ ነው ብለዋል። የአካባቢ ስነ ምህዳርን ወደ ነበረበት የመመለስ፣ ዘላቂ እድገትና የማይበገር አቅም ለመገንባት ያላትን ጠንካራ ቁርጠኝነት የሚያመላክትና ለዚህም ስራዋ እውቅና የሰጠ መሆኑን አመልክተዋል። አረንጓዴ ዐሻራ እና የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያ አረንጓዴ ልማት ስራ ማሳያዎች እንደሆኑም ነው የተናገሩት። ኮፕ 32 ለኢጋድ ቀጣና ወሳኝ መድረክ መሆኑን ገልጸው ተቋሙ ድርቅ፣ የአየር ንብረት ለውጥ የፈጠረው የዜጎች መፈናቀልና የውሃ እጥረትን ጨምሮ ሌሎች አንገብጋቢ አጀንዳዎች የበለጠ ትኩረት እንዲሰጣቸው እንደሚያደርግ አመልክተዋል። ኢጋድ ከኢትዮጵያ፣ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ማዕቀፍ ጽህፈት ቤት(UNFCCC Secretariat) እና ዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በመሆን ጉባኤው ሁሉን አሳታፊ፣ የአፍሪካ የቅድሚያ ትኩረቶች ማዕከል ያደረገና ለአየር ንብረት ለውጥ ዘላቂ መፍትሄ የሚገኝበት እንዲሆን በትብብር እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። በብራዚል ቤለም እየተካሄደ የሚገኘው 30ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 30) ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2027 የሚካሄደውን ኮፕ 32 ጉባኤ እንድታስተናግድ መመረጧ ይታወቃል። የአፍሪካ ሀገራት ለኢትዮጵያ የኮፕ 32 የማስተናገድ ፍላጎት ሙሉ ይሁንታቸውን ሰጥተዋል።
ኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 32)ን እንድታስተናግድ መመረጧ ለኢትዮጵያ እና ለአፍሪካ ታሪካዊ ነው - የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር
Nov 15, 2025 197
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 32)ን እንድታስተናግድ መመረጧ ለኢትዮጵያ እና ለአፍሪካ ታሪካዊ ነው ሲሉ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። ሊቀ መንበሩ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ32)ን እንድታስተናግድ በመመረጧ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ጉባኤውን የማስተናገድ ውሳኔው ለኢትዮጵያ እና ለአፍሪካ ታሪካዊ መሆኑን ሊቀመንበሩ ገልጸው ይህም አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ እርምጃ ያላትን የማይናወጥ ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል። ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አማካኝነት እያሳየች ያለውን የአየር ንብረት የመሪነት ሚናም አድንቀዋል። ኢትዮጵያ መጠነ ሰፊ የደን መልሶ ልማት እና አረንጓዴ ዐሻራን ጨምሮ ጠንካራ የአካባቢ ጥበቃ እርምጃዎችን እየወሰደች እንደምትገኝ አመልክተዋል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ሁነቶችን በስኬት በማስተናገድ እምቅ አቅም እንዳላት አንስተው ከፍተኛ ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ ጉባኤዎችን ለማዘጋጀት ጠንካራ ተቋማዊ አቅም እና ልምድ አላት ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት ዋና መቀመጫ እና የዓለም የዲፕሎማሲ ማዕከል የሆነችው አዲስ አበባ ጉባኤውን እንድታስተናግድ መመረጧ በዓለም አቀፍ ትብብር ያላትን ማዕከላዊ ሚና የበለጠ እንደሚያሳድገውም ገልጸዋል። ኮሚሽኑ ከኢትዮጵያ፣ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ማዕቀፍ(UNFCCC) እና አጋሮች ጋር በመሆን(ኮፕ 32) ሁሉን አካታችና ውጤታማ በማድረግ የአፍሪካን የአየር ንብረት የቅድሚያ ትኩረቶች የበለጠ ለማራመድና ዓለም አቀፍ አጋርነት ለማጠናከር በቅርበት እንደሚሰራ መግለጻቸውን ህብረቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል። በብራዚል ቤለም እየተካሄደ የሚገኘው 32ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ጉባኤ(ኮፕ 30) ኢትዮጵያ እ.አ.አ በ2027 የሚከናወነውን ኮፕ 32 እንድታስተናግድ ተመርጣለች። የአፍሪካ ሀገራት ለኢትዮጵያ የኮፕ 32 የማስተናገድ ፍላጎት ሙሉ ድጋፋቸውን መስጠታቸው ይታወሳል።
ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የጋራ ርምጃን የሚያበረታታ ውጤት ለማምጣት ቁርጠኛ ናት - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Nov 14, 2025 202
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 5/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ በኮፕ 32 መድረክ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የጋራ ርምጃን የሚያበረታታ ጠንካራ እና ትርጉም ያለው ውጤት ለማምጣት ሙሉ በሙሉ ቁርጠኛ መሆኗን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አረጋገጡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ ኮፕ 32ን እንድታስተናግድ ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ትልቅ ኃላፊነት ስለሰጠን ክብር ይሰማናል ብለዋል። አፍሪካ በ2025 በተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ኮንፈረንስ (COP 30) ላይ በብራዚል በአንድ ድምጽ ተናግራለች፤ ዓለምም አዳምጧል ብለዋል። እንዲሁም ኢትዮጵያ በፈረንጆቹ በ2027 በአዲስ አበባ COP 32ን ለማስተናገድ ያቀረበችውን ጥያቄ ሙሉ በሙሉ ለደገፉ የአፍሪካ ሀገራት ተወካዮች ምሥጋና አቅርበዋል። በሰው ልጆች ኑሮ በጣም አንገብጋቢ ከሆኑት ተግዳሮቶች መካከል አንዱን ለመቅረፍ እንዲቻል የጋራ ጥረቶችን ለመምራት ዕድሉን ስላገኘንም አመሥጋኞች ነን ብለዋል። ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ይህን ትልቅ ኃላፊነት ስለሰጠንም ክብር ይሰማናል ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ይህ ዕውቅና ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ላይ ያላትን ቁርጠኛ ርምጃ፣ አመራር ብሎም ዋና ዋና ዓለም አቀፍ ዝግጅቶችን የማስተናገድ የዳበረ ዐቅም ያሳያል ሲሉም በአጽንኦት ገልጸዋል። በመሆኑም ኢትዮጵያ በምታስተናግደው የኮፕ 32 መድረክ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የጋራ ርምጃን የሚያበረታታ ጠንካራ እና ትርጉም ያለው ውጤት ለማምጣት ሙሉ በሙሉ ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች ላይ የበጋው ደረቅ፣ፀሐያማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ ይቀጥላል
Nov 12, 2025 250
አዲስ አበባ፤ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦በሚቀጥሉት አስር ቀናት በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች ላይ የበጋው ደረቅ፣ፀሐያማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፥ በሰሜን፣በሰሜን ምስራቅ፣ በምስራቅ፣ መካከለኛው እና ደቡብ ደጋማ አካባቢዎች ላይ የሌሊቱና የማለዳው ቅዝቃዜ እንደሚቀጥል አስታውቋል። በጋ ሁለተኛ የዝናብ ወቅታቸው የሆኑት የደቡብ፣ደቡብ ምስራቅ እና የደቡብ ምዕራብ የአገሪቱ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ የሚቲዎሮሎጂ መረጃዎች ያሳሉ ብሏል። ወቅቱን ያልጠበቀ አነስተኛ መጠን ያለው ዝናብ በሰሜን፣ መካከለኛው፣ ምዕራብና ደቡብ ጎንደር ዞኖች፣ባህርዳር ዙሪያ፣ አዊ፣ በምዕራብና ምስራቅ ጎጃም፣ መተከል፣ አሶሳ፣ ካማሺ፣አርሲ፣በባሌ ዞኖች አልፎ አልፎ ሊዘንብ እንደሚችል ኢኒስቲትዩቱ ገልጿል። በሚቀጥሉት አስር ቀናት በደቡብ ምዕራብ እና ደቡባቢ የአገሪቱ ክፍሎች ላይ የሚኖረው መካከለኛ መጠን ያለው ርጥበት ለወቅቱ የግብርና ስራ እንቅስቃሴ በአመዛኙ አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው አስታውቋል። የበጋ ርጥበት ተጠቃሚ ተፋሰሶች መጠነኛ የገፀ ምድር የውሃ ፍሰት እንደሚኖራቸው የሚጠበቅ ሲሆን የተቀሩት ዝቅተኛ ርጥበት እንደሚኖራቸው ገልጿል። በዚህም አብዛኛው ባሮ አኮቦ፣ መካከለኛው እና ታችኛው ኦሞ ጊቤ፣ ስምጥ ሸለቆ፣ አባይ እንዲሁም ገናሌ ደዋ መካከለኛ ርጥበት ያገኛሉ፡፡ አብዛኛው አዋሽ፣ዋቤ ሸበሌ፣አፋር ደናክል፣ተከዜ፣ ኦጋዴን ደግሞ ከመጠነኛ ርጥበት እስከ ደረቅ ሁኔታ ይኖራቸዋል ተብሏል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም