አካባቢ ጥበቃ
የጋምቤላ ክልል ምክር ቤት አባላት የተራቆቱ አካባቢዎችን በደን ለመሸፈን ሕዝቡን በማስተባበር የበኩላቸውን ሊወጡ ይገባል -አፈ ጉባዔ ባንቻየሁ ድንገታ
Jul 27, 2024 115
ጋምቤላ፤ ሐምሌ 20/2016(ኢዜአ)፦የጋምቤላ ክልል ምክር ቤት አባላት የተራቆቱ አካባቢዎችን በደን ለመሸፈን ሕዝቡን በማስተባበር የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ባንቻየሁ ድንገታ አሳሰቡ። የክልሉ ምክር ቤት አባላት በጋምቤላ ወረዳ ቃርሚ ቀበሌ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ዛሬ አካሂደዋል።   ዋና አፈ-ጉባኤዋ በመርሃ ግብር ላይ እንዳሳሰቡት የምክር ቤቱ አባላት ሕዝቡን በማስተባበር የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብርን ለማሳካት መትጋት አለባቸው። በተለይም በክልሉ የተራቆቱ አካባቢዎችን በደን ለመሸፈን ሕዝቡን በማስተባበር መስራት እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። በተጨማሪም በበጎ ፈቃድ አገልግሎት የሚካሄዱ የአቅም ደካሞችና የአረጋውያን መኖሪያ ቤቶች እድሳትና ሌሎች ሥራዎችንም አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል ብለዋል። በቀጣይም በተዋረድ በሚገኙ የዞንና የወረዳ ምክር ቤቶች አባላት በተመሳሳይ ሁኔታ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር እንደሚያካሂድ አፈ ጉባኤዋ አስታውቀዋል። የክልሉ ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ መሰረት ማቲዎስ፣ በበኩላቸው በችግኝ ተከላ የተሳተፉት የክልሉን ደን ሃብት ወደቀደመው ደረጃ ለመመለስ የሚደረገውን ጥረት ለማሳካት ነው ብለዋል። በቀጣይም ችግኞችን በመንከባከብ እንዲጸድቁ የድርሻቸውን መወጣት እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በክረምቱ ወራት በአረንጓዴ አሻራ ልማትና በሌሎችም የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራዎች በንቃት እንደሚሳተፉ የተናገሩት ደግሞ ሌላው የክልሉ ምክር ቤት አባል አቶ ኡጀሉ ኝጊዎ ናቸው።    
በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ ልማት ከ53 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በችግኝ ይሸፈናል
Jul 27, 2024 65
መቀሌ፤ ሐምሌ 20/2016(ኢዜአ)፦በትግራይ ክልል በክረምት ወራት በአረንጓዴ አሻራ ልማት ንቅናቄ ከ53 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በችግኝ እንደሚሸፈን በጊዜያዊ አስተዳደሩ የእርሻና ተፈጥሮ ሃብት ቢሮ ገለጸ። በቢሮው የደን ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ ተስፋይ ተክለሃይማኖት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ ልማት የሚተከለውን ችግኝ ለመንከባከብ እና ለመጠበቅ የተከላ ካርታ ተዘጋጅቶ እየተሰራ ነው፡፡ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የፍራፍሬ ችግኞችን ጨምሮ የደን ሽፋንን ለማሳደግ፣ የከተማ ውበት ለመጨመር እና ስነ ምህዳርን ለመጠበቅ የሚያስችሉ ችግኞች እየተተከሉ መሆናቸውን አብራርተዋል። በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ ልማት ከ53 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ የሚሆን ቦታን ለመሸፈን 33 ሚሊዮን ችግኞች መዘጋጀታቸውንና ወደ ተግባር መገባቱን ገልፀዋል። እስከ አሁን 19 ሚሊዮን 668 ሺህ ችግኞች በተዘጋጀላቸው ቦታ ላይ እንደተተከሉም ተናግረዋል፡፡ የከተማና የገጠር ነዋሪ ማህበረሰብ፣ የመንግስትና የግል ሰራተኞች፣ የስፖርት ማህበረሰብ እና የተለያዩ ማህበራት እንዲሁም የጸጥታ አካላት በችግኝ ተከላ መርሐ ግብሩ ላይ ተሳትፎ እያደረጉ መሆናቸውን አቶ ተስፋይ ተናግረዋል፡፡ በዚህም የተያዘውን እቅድ ለማሳካት ሰፊ ርብርብ እየተደረገ መሆኑንም ገልጸዋል። ክልሉ ከፌዴራል መንግስት ጋር በመተባበር ነሐሴ 13 ቀን 2016 ዓ/ም በአንድ ጀምበር 900 ሺህ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ የብዘት ወረዳ የተፈጥሮ ሃብት አስተባባሪ አቶ መንግስቱ ጸጋይ በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች ሳቢያ የተጎዱና የተራቆቱ አካባቢዎችን አረንጓዴ ለማልበስ እና ተፈጥሮን ለመጠበቅ ችግኝ መትከል እንደ ባህል ሊወሰድ ይገባል ብለዋል፡፡ በወረዳው ማህበረሰቡን ያሳተፈ የተከላ መርሐ ግብር እየተከናወነ መሆኑን እና ተራሮችን በማልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ የማይጨው ከተማ ነዋሪ ወጣት አበበ ዘነበ ችግኝ መትከል ለነገ የተሻለ ህይወት መሰረት መጣል ነው" ብላለች፡፡ በዚህም በሚዘጋጁ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብሮች የመትከል እና የመንከባከብ ስራዎችን እየሰራን ነው ብላለች፡፡ ታሕታይ ቆራሮ ወረዳ የውህደት ቀበሌ ነዋሪ ወጣት ብርሃነ ሃይለ የተተከሉ ችግኞችን ከእንስሳት ንክኪ ነጻ በማድረግ በመንከባከብ ላይ መሆናቸውን ገልጿል፡፡
በአማራ ክልል ከተሞችን በአረንጓዴ በማልማት ምቹና ሳቢ የማድረጉን ተግባር ማጠናከር ይገባል- ዶክተር አህመዲን መሐመድ
Jul 26, 2024 194
ደሴ ፤ ሐምል 19/2016(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ከተሞች በክረምቱ ችግኞችን በስፋት በመትከል በአረንጓዴ ማልማት፣ ምቹና ሳቢ የማድረጉን ተግባር ማጠናከር እንደሚገባ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ከተሞች ልማት ክላስተር አስተባባሪና የከተሞችና መሰረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አህመዲን መሐመድ ገለጹ። ዶክተር አህመዲን መሐመድን ጨምሮ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራር አባላት በደቡብ ወሎ ዞን ሐይቅ ከተማ ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል።   በዚህ ወቅት ዶክተር አህመዲን እንዳመለከቱት፤ በክልሉ ከተሞችን በአረንጓዴ አሻራ ችግኝ በማልማት ምቹና ሳቢ የማድረጉ ተግባር አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል። ለዚህም በየከተሞቹ ሁሉም ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራውን ማሳረፍ እንዳለበት መልዕክት አስተላልፈዋል። የአመራር አባላቱ በሐይቅ ከተማ ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር የተለያዩ የልማት እንቅስቃሴዎችን ጎብኝተዋል።
አካባቢን ጽዱና ማራኪ በማድረጉ እንቅስቃሴ የሴቶችና የወጣቶች ተሳትፎ ዘላቂ እንዲሆን ሊጉ አስገነዘበ
Jul 25, 2024 173
ሚዛን አማን ፤ ሐምሌ 18/2016(ኢዜአ)፦ ከተሞችንና የመኖሪያ አካባቢን ጽዱና ማራኪ በማድረጉ እንቅስቃሴ ሴቶችና ወጣቶች ዘላቂ ተሳትፎ ሊያደርጉ እንደሚገባ የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የሴቶች ሊግ አስገነዘበ። የብልጽግና ፓርቲ ሴቶች ሊግ "በጎነት ለእህትማማችነት" በሚል በመሪ ቃል የክረምትና የበጋ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት የጽዳት ዘመቻ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ሚዛን አማን ከተማ ዛሬ አከናውኗል። በዚህ በወቅት የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የሴቶች ሊግ አደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ወይዘሮ አሰለፈች ታደሠ እንደተናገሩት፤ ውብና አረንጓዴ አካባቢን ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ሴቶችና ወጣቶች ባህል አድርገው በዘላቂነት ሊሳተፉ ይገባል።   በዘመቻ መልክ ከሚደረገው የጽዳት መርሃ ግብር ባሻገር ሴቶችና ወጣቶች በየጊዜው ኃላፊነት ወስደው የማጽዳት ተግባሩን ሊያከናውኑ ይገባል ብለዋል። የመኖሪያ ቤት ዙሪያን በግል ከማስዋብ ጀምሮ ከጎረቤት ጋር ተቀናጅቶ አካባቢን ማጽዳት ለኑሮ ምቹ መንደርን ለመፍጠር የሚያስችል ተግባር በመሆኑ ሁሉም ትኩረት እንዲሰጠውም አሳስበዋል። ''አሁን ላይ እንደ ሀገር በጋራ ከምንዘምትባቸው መልካም መስኮች አንዱ የአካባቢ ጽዳት ነው ያሉት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊዋ ለዚህ ስኬታማነት በቁርጠኝነት ልንሳተፍ ያስፈልጋል'' ብለዋል። በሁሉም የሀገራችን አካባቢዎች ጤንነቱ የተጠበቀ ማኅበረሰብን ለመገንባት ህብረተሰቡን ያሳተፈ ጠንካራ እንቅስቃሴ በፓርቲ ደረጃ እየተካሄደ እንደሚገኝም አመላክተዋል።   የክልሉ ንግድና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ብዙነሽ ዘብዴዎስ በበኩላቸው ሁሉም አካል ለቀጣይ ትውልድ ጽዱና አረንጓዴ አካባቢን ለማስረከብ ሊተጋ ይገባል ብለዋል። ወቅቱ ክረምት ከመሆኑ የተነሳ የጎርፍ መፋሰሻ ቱቦዎች በቆሻሻ ሊደፈኑ እንደሚችሉ ጠቁመው ይህ እንዳይሆን አስቀድሞ ቆሻሻን በማስወገድ የከተማን ደህንነት መጠበቅ አስፈላጊ እንደሆነ አስገንዝበዋል። በከተማዋ ከማኅበረሰቡ ጋር በሳምንታዊ የጽዳት መርሃ ግብር በመሳተፍ የበኩላቸውን ኃላፊነት እንደሚወጡም ገልጸዋል። በከተማ የጽዳት መርሃ ግብሩ ላይም ከብልጽግና ፓርቲ ዋናው ጽህፈት ቤት፣ ከክልል፣ ከዞን ሴቶች ሊግ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።    
የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን በዘላቂነት ለመቋቋም ቅድመ ማስጠንቀቂያ ላይ በትኩረት መሠራት አለበት 
Jul 24, 2024 289
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2016 (ኢዜአ)፦ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን በዘላቂነት ለመቋቋም የቅድመ ማስጠንቀቂያ መረጃዎችን መሠረት ያደረጉ እርምጃዎች ላይ በትኩረት መሥራት እንደሚገባ ተጠቆመ። በዓለም አቀፉ የእንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩት የአየር ንብረት ዘርፍ ተመራማሪ ተፈሪ ደጀኔ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ዓለም በከፍተኛ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ ሥር ወድቃለች። ከፍተኛ የሆነ የሙቀት መጨመር፣ የዝናብ ሥርጭት መጠን ማነስ፣ ድርቅ፣ ጎርፍና ሌሎችም ተያያዥ ተግዳሮቶች በሰውና በእንስሳት ላይ የተለያዩ ተጽዕኖዎችን እያደረሱ መሆኑን ነው የገለጹት። በተለይም ኢንስቲትዩቱ ትኩረት አድርጎ በሚሰራው የቁም እንስሳት፣ ድርቅ በሚከሰትበት ጊዜ በውኃና በመኖ እጥረት እንዲሁም እንስሳቱ በቀላሉ ለበሽታ ተጋላጭ በመሆን ለከፍተኛ ጉዳት እየተዳረጉ መሆኑን ጠቁመዋል። ይህንንም ከፍተኛ ተጽዕኖ ለመቋቋም የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራዎች ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ ዓለም አቀፉ የእንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩት ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራዎች ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም ከሚረዱ ዋነኛ ጉዳዮች በቅድመ ማስጠንቀቂያ ላይ በቂ ሥራ መሥራት መሆኑን በማንሳት፤ በዚሁ ላይ የሚመለከታቸው አካላት በትኩረት መሥራት እንደሚገባቸው ምክረ-ኃሳብ ሰጥተዋል። ኢንስቲትዩቱ በዓለም ባንክ በኩል በሚደረግ ድጋፍ በስድስት የአፍሪካ አገራት በዝቅተኛ ሥፍራዎች በርካታ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽና ሌሎች ተጓዳኝ የምርምር ሥራዎችን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ከእነዚህም ውስጥ ኢትዮጵያ አንዷ መሆኗን በማንሳት፤ የተለያዩ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም በዋናነትም በአየር ንብረት መረጃዎች ላይ በቂ እውቀት ለመስጠትና የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራዎች ለኅብረተሰቡ ተደራሽ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል። በዚህ ረገድ፤ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት መረጃን ተደራሽ በማድረግ የሚጠበቅባቸውን ሚና ሊወጡ እንደሚገባ ጥሪ አቅርበዋል። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር የአየር ንብረት ተጽዕኖን ለመቋቋም እየወሰደች ያለው እርምጃም የሚበረታታ መሆኑንም ተናግረዋል። ዓለም አቀፉ የእንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩት (ኢልሪ) እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር 1974 አንስቶ በኢትዮጵያ እየሰራ የሚገኝ ተቋም ነው።    
በድሬዳዋ አስተዳደር በቤተሰብ ደረጃ የፍራፍሬ ችግኞችን የመትከል መርሃ ግብር ዛሬ ተጀመረ
Jul 24, 2024 171
ድሬዳዋ፤ ሐምሌ 17/2016 (ኢዜአ)፦ በድሬዳዋ አስተዳደር የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካል የሆነው በቤተሰብ ደረጃ የፍራፍሬ ችግኞችን የመትከል መርሃ ግብር ተጀምሯል። የዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር አካል የሆነው "አንድ ሎሚ ለአንድ ቤተሰብ" በሚል መሪ ሃሳብ የቤት ለቤት የፍራፍሬ ችግኞች ተከላው በአስተዳደሩ በወረዳ ሁለት ነው የተጀመረው። በመርሃ ግብሩ ላይ ከንቲባ ከድር ጁሃርን ጨምሮ የአስተዳደሩ ከፍተኛ የአመራር አካላት የሎሚ፣ ፓፓያ፣ ማንጎ፣ ዘይቱን፣ ጊሽጣ፣ መንደሪን፣ ብርትኳን፣ አፕል እና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞችን ተክለዋል።   የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኑረዲን አብደላ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ድሬዳዋ ለከተማ ግብርና እና ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ምቹና ተስማሚ ናት።   ነዋሪዎች ለዘመናት በግቢያቸው ውስጥ የተለያዩ ፍራፍሬዎችን በማብቀል ያከበቱትን ልምድ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሩ ይበልጥ የማጠናከር ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። ባለፉት የአረንጓዴ አሻራ ዘመቻዎች የተተከሉት የፍራፍሬ ችግኞች ፍሬ መስጠት መጀመራቸውን ጠቅሰው፤ ይህም የቤተሰብ ፍጆታ ከመቻል በዘለለ ለተጨማሪ የገቢ ምንጭ እየዋለ ይገኛል ብለዋል። በአስተዳደሩ የገጠር ወረዳ ነዋሪዎችም በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የተጀመሩትን ስራዎች ስኬታማ በማድረግ ተጨባጭ ውጤቶች እየተገኙ መሆናቸውን አቶ ኑረዲን ገልጸዋል። ዛሬ "አንድ ሎሚ ለአንድ ቤተሰብ" በሚል መሪ ሃሳብ የተጀመረው የፍራፍሬ ችግኞች ተከላ የተገኙ ውጤቶችን ይበልጥ ለማሳደግ እና የፍራፍሬ ዋጋን ለማረጋጋት ያስችላልም ብለዋል። ዘንድሮ በአረንጓዴ አሻራ ከሚተከሉ ችግኞች መካከል ለምግብነት እና ለገቢ ምንጭነት የሚያገልግሉ የፍራፍሬ ችግኞች እንደሚገኙበትም ተናግረዋል።   በተያያዘ ዜና በድሬዳዋ አስተዳደር ቃልቻ ገጠር ቀበሌ የተለያዩ የገጠር ማህበረሰብ እና የአመራር አካላት የተሳተፉበት የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ ተካሂዷል። በስነስርዓቱ ላይ የአስተዳደሩ ግብርና፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ መሐመድአሚን ኡመር ተገኝተዋል። አቶ መሐመድአሚን በዚሁ ወቅት የአረንጓዴ አሻራ ዘመቻ ለድሬዳዋ ጎርፍን በመከላከል፣ የተፈጥሮ ሀብትን በመጠበቅ፣ የአየር ንብረት ለውጥን በመመከትና የቤተሰብ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ዓይነተኛ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ገልጸዋል። ዘንድሮም የተገኙ ውጤቶችን ለማጠናከር የተቀናጀ ዘመቻ እየተካሄደ መሆኑን በማውሳት።  
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የትናንት፣ የዛሬ እና የነገን ትውልድ የሚያስተሳስር የእድገትና ብልጽግና መሠረት ነው - አቶ አደም ፋራህ
Jul 24, 2024 159
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2016(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የትናንት፣ የዛሬ እና የነገን ትውልድ የሚያስተሳስር የሀገር እድገትና ብልጽግና መሠረት መሆኑን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ሃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህ ገለጹ። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ኢትዮጵያ ምቹ ፕላኔት የመፍጠር ሚናዋን በብቃት እየተወጣችበት ያለ ግዙፍ ኢኒሼቲቭ መሆኑንም ተናግረዋል። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ሃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህ፤ የፓርቲው ዋና ጽህፈት ቤት ከፍተኛ አመራሮችና ሠራተኞች በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ችግኞችን ተክለዋል።   በመርሃ-ግብሩ ላይ አቶ አደም ባደረጉት ንግግር፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር የትናንት፣ የዛሬ እና የነገን ትውልድ የሚያስተሳስር የእድገትና ብልጽግና መሠረት መሆኑን ገልፀዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ኢትዮጵያ ምቹ ፕላኔት የመፍጠር ሚናዋን በብቃት እየተወጣች ያለ ግዙፍ ኢኒሼቲቭ መሆኑን ተናግረዋል። የልማት ሥራው ትላንት የተሰሩ ታሪኮችን የማስቀጠል፣ አደጋዎችን በዘላቂነት የመከላከልና ምድርን ከአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ መጠበቅ የሚያስችል ነው ብለዋል። ለሥራ ዕድል ፈጠራ፣ ምርታማነትን ለማሳደግና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ገልፀዋል። ኢትዮጵያውያን በጋራ እየተገበሩት ያሉትን ሀገርን አረንጓዴ የማልበስ ሥራ ማጠናከር እንዳለባቸው ገልጸው፤ ብልጽግና ፓርቲ ለመርሃ-ግብሩ መሳካት የመሪነት ሚናውን እየተወጣ ይቀጥላል ብለዋል። በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ሞገስ ባልቻ፤ አዲስ አበባን ምቹ፣ ውብና አረንጓዴ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልፀዋል።   በብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለሰ ዓለሙ፤ የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብሩ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ የጀርባ አጥንትና የኢትዮጵያውያን የጋራ አጀንዳ ሆኗል ብለዋል።   በሁሉም የህይወት መስክ ጉልህ ፋይዳ ያለውን ይህን የአረንጓዴ ልማት ኢትዮጵያ በአርዓያነት እየከወነች ነው ያሉት ኃላፊው፤ ይህንን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉም ተናግረዋል። የፓርቲው የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ሳዳት ነሻ፤ አረንጓዴ አሻራ ችግኝ ከመትከል በላይ ሀገርን አረንጓዴ የማልበስና ምርታማነትን የማሳደግ ጉዳይ መሆኑን ገልፀዋል።   ኢትዮጵያውያን ከሚያለያዩ ነገሮች ይልቅ የሚያሰባስቡና ሀገርን የሚያሻግሩ ጉዳዮች ላይ በማተኮር በሁሉም መስክ የፀናች ሀገርን ለተተኪው ትውልድ የማስረከብ የጋራ ዓላማን ማሳካት አለባቸው ብለዋል። የፓርቲው የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ምክትል ኃላፊ ሙሳ አህመድ፤ ብልጽግና ፓርቲ የሀገርን ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ ለአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት ልዩ ትኩረት መስጠቱን ገልፀዋል። በዚህም በገጠርና ከተማ ሁለንተናዊ ፋይዳ እየሰጠ የሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ተጠናክሮ መጠቀሉን ጠቅሰው፤ ችግኝ ከመትከል ባለፈ በመንከባከብ ለፍሬ ማብቃት የሁሉም ኃላፊነት ሊሆን ይገባል ብለዋል። የለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ታረቀኝ ገመቹ፤ በክፍለ ከተማው የአረንጓዴ ልማትና ውብ ከባቢን የመፍጠር ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመዋል።
ወጣቱ ከአረንጓዴ አሻራ ልማት ጎን ለጎን ለዘላቂ ሰላም መስፈን ሊሰራ ይገባል -የብልጽግና ፓርቲ የወጣቶች ሊግ
Jul 24, 2024 139
ደብረ ብርሀን ፤ሐምሌ 17/2016 (ኢዜአ)፦ ወጣቱ ከአረንጓዴ አሻራ ልማት ጎን ለጎን ለዘላቂ ሰላም መስፈን መስራት እንዳለበት የብልጽግና ፓርቲ የወጣቶች ሊግ አስገነዘበ። በደብረ ብርሃን ከተማ "በጎነትና አብሮነት ለኢትዮጵያ ከፍታ "በሚል መሪ ሃሳብ የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ማስጀመሪያ የአረጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ተከናውኗል።   በብልጽግና ፓርቲ ወጣቶች ሊግ ዋና ጽህፈት ቤት የፖለቲካ ዘርፍ ሀላፊ ወጣት ሰብለ በቀለ እንደገለፀችው መንግስት የዜጎችን ሰላም ለማስጠበቅና የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እየሰራ ነው። የኢትዮጵያ የከፍታ ዘመን በጠንካራ መሰረት ላይ ለማቆም በመንግስት የተጀመሩ የልማትና የሰላም ስራዎች ላይ ተግቶ መስራት እንደሚገባ አስገንዝባለች። በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ጎን ለጎን ለዘላቂ ሰላም መስፈን የውይይትና የምክክር ባህልን ማጎልበት እንደሚገባ ተናግራለች።   "በተያዘው የክረምት ወራት በመላ ሃገሪቱ በርካታ የሊጉ አባላት ወጣቶች በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተሰማርተው እየሰሩ ነው" ብላለች። በብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል ወጣቶች ሊግ ሀላፊ ወጣት ተስፋሁን ተሰማ በበኩሉ "የክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት አንድነትን በማጠናከር ሁለተናዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ያግዛል" ብሏል። በተያዘው ክረምት በክልሉ አባላትን በማስተባበር ችግኞችን በመትከል የአረጓዴ አሻራ መርሀ ግብርን የመደገፍ ስራ እየተከናወነ ነው" ብሏል። በተጨማሪም 3 ሺህ የአረጋዊያንን መኖሪያ ቤቶችን ጥገናና አንድ ሺህ ቤቶች ደግሞ በአዲስ ለመስራት እንዲሁም 4 ሺህ ዩኒት ደም ለመሰብሰብ ታቅዶ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን አመልክቷል።   "ለአስር ሺህ ተማሪዎች የማጠናከሪያ ትምህርት እንደሚሰጥ ጠቅሶ " 20 ሺህ ደርዘን ደብተርና 5 ሺህ ፓኬት እስክሪብቶ በማሰባሰብ በአነስተኛ ገቢ ለሚተዳደሩ ቤተሰቦች ልጆች ድጋፍ ይደረጋል" ሲል አክሏል። የክልሉን ሰላም በዘላቂነት ለማረጋገጥ በምክክር ችግሮች እንዲፈቱ ውይይቶች እንደሚካሄዱም ተናግሯል። "የተራቆቱ መሬቶችን በአረንጓዴ ለማልበስ የክረምት ችግኝ ተከላ በልዩ ትኩረት እየተከናወነ ነው" ያሉት ደግሞ የደብረ ብርሀን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት ናቸው።   ወጣቶች በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ፥ በችግኝ ተከላ፣ የአቅመ ደካማ ቤቶችን በመጠገን፣ በደም ልገሳና በወንዝ ዳር ልማት በመሳተፍ ሀላፊነታቸውን እየተወጡ ነው ብለዋል። በአንድነት ከተባበርን ሰላማችንን ከማስጠበቅ ጎን ለጎን አረንጓዴ አሻራ ልማታችንን ለማስቀጠልና ከተረጅነት ለመላቀቅ አቅም አለን ብለዋል። በከተማ አስተዳደሩ በተያዘው ክረምት ለደን፣ ለከተማ ውበትና ለምግብነት የሚያገለግሉ ችግኞች ተዘጋጅተው ተከላ እየተከናወነ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ከወሰን ተሻጋሪ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች መካከል ተማሪ ሀይሌ ጋጭቶ በበኩሉ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፥ ስራን ከመልመድ ባሻገር ማህበራዊ መስተጋብሮችን እንድንወራረስ አግዞናል ብሏል። "በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ወጣቶችን እርስ በእርስ በመተዋወቅ ለሀገራዊ እሴት ግንባታ ተባብረን እንድንሰራ አግዞናል" ያለችው ደግሞ የደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪ በጎ ፍቃደኛ ወጣት ቢታኒያ በትሩ ናት። በአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ በየደረጃው የሚገኙ አመራሮችና በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች እየተሳተፉ ነው።  
በጋምቤላ ክልል እየተካሄደ ላለው የአረነጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ስኬታማነት የህብረተሰቡ ተሳትፎ ሊጠናከር እንደሚገባ ተመለከተ
Jul 24, 2024 79
ጋምቤላ ፤ ሐምሌ 17/2016 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል እየተካሄደ ላለው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ስኬታማነት የህብረተሰቡ ተሳትፎ ሊጠናከር እንደሚገባ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ተወካይ አቶ ጁል ናንጋል አመለከቱ። የክልሉ ሴክተር መስሪያ ቤት ሰራተኞች በጋምቤላ ወረዳ ቃርሚ ቀበሌ ዛሬ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሂደዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ተወካይ አቶ ጁል ናንጋል በዚሁ ወቅት እንዳሉት የአረንጓዴ አሻራ የአሁኑን ትውልድ ብቻ ሳይሆን መጪውን ትውልድ የሚታደግ ልማት ነው።   ይህን ታሰቢ በማድረግ መንግስት እንደ ሀገር ብሎም እንደ ክልል የአረንጓዴ አሻራ ልማት በማጠናከር የግብርና ስራውን ለማሳላጥ በትኩረት እየሰራ ነው ብለዋል። በመሆኑም በክልሉ እየተካሄደ ላለው የአረንጓዴ አሻራ ልማት ስኬታማነት ህዝቡ ሁለንተናዊ ተሳትፎውን በመጠናከር አሻራውን ሊያሳርፍ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የክልሉ ሴክተር መስሪያ ቤቶች ሠራተኞች በዕለቱ የተከሏቸውን ችግኞች በመንከባከብ ረገድም ተሳትፏቸውን እንዲያጠናከሩ ተወካዩ አሳስበዋል። የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ኡጀሉ ሉዋል በበኩላቸው በክልሉ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ከክልል እስከ ወረዳ ያሉት የመንግስት ሰራተኞችን ጨምሮ ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ እየተካሄደ ነው ብለዋል።   የችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት በአግባቡ እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመው፤ ነሐሴ 13 ቀን 2016 ለሚካሄደው የአንድ ጀመር የችግኝ ተካላ መርሃ ግብር አስፈላጊው ዝግጅት እየተካሄደ መሆኑንም ገልጸዋል። በዕለቱ በተካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ላይ ሲሳተፉ ያገኘናቸው የእድሜ ባለጸጋ አቶ ኡቦንግ ሉዋል በሰጡት አስተያየት በችግኝ ተከላ መርሃ ግብር እየተሳተፉ ያለው ለራሳቸው ሳይሆን ለመጪው ትውልድ አሻራቸውን ለማስቀመጥ በማሰብ መሆኑን ተናግረዋል። አሁን ላይ እየተከሉ ያሉት ችግኞች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ስለሆኑ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጭምር እንደሚያግዙ እምነታቸውን ገልጸዋል። በእለቱ በተካሄደው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የክልል ሴክተር መስሪያ ቤት ሰራተኞች ተሳተፈዋል።  
በክረምት ወቅት የሚኖረው ከባድ ዝናብ በተፋሰስ አካባቢ ጉዳት እንዳያደርስ ከወዲሁ ጥንቃቄ ሊደረግ ይገባል - የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት
Jul 24, 2024 85
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2016(ኢዜአ)፦ በክረምት ወቅት የሚኖረውን ከባድ ዝናብ የጎርፍ አደጋ ስጋት ባለባቸው የተፋሰስ አካባቢዎችና በሌሎችም ጉዳት እንዳያደርስ ከወዲሁ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አሳሰበ። የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ በአዋሽ፣ በአባይ፣ በባሮ አኮቦና በመሳሰሉት ተፋሰሶች ላይ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግ ትንበያው ያመለክታል። የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የሀገሪቱ አካባቢዎች ከመጠን በላይና ጎርፍ የሚያስከትሉ ከባድ ዝናብ እንደሚኖራቸውም ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል። በኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት የጎርፍ አደጋ በተፋሰስ፣ በከተሞችና በረባዳማና ሸለቋማ ሥፍራ የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ጉዳት ሲያደርስ ይታወቃል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ እነዚህን ችግሮች አስቀድሞ በመከላከልና በሚወሰደው የጥንቃቄ እርምጃ ጉዳቱን መቀነስ የሚያስችል ሥራ ቢሰራም በቀጣይም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት መክሯል። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የምታስተናግዳቸውን ወቅቶች በመለየት ትንበያ የሚሰጥ ሲሆን፤ በዘንድሮ የክረምት ወቅት ሊኖር የሚችለውን ትንበያ በግንቦት ወር ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ተሰጥቷል። ኢንስቲትዩቱ በፍጥነት እና በተደራጀ መልኩ መረጃ የሚያደርሱ ዘመናዊ የሚቲዎሮሎጂ መረጃ መሰብሰቢያ የመሠረተ-ልማት አውታሮችን የማስፋት ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። የዘንድሮን ክረምት የሚወስነውን ዓለም አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ ክስተት ከግምት ውስጥ በማስገባትም የላሊና ተጽዕኖ ሥር እንደሚሆን መተንበዩን ተናግረዋል። ይህም በክረምት ዝናብ ተጠቃሚ አካባቢዎች ከባድ ዝናብ እንደሚኖር ትንበያው ማመልከቱን ገልጸው፤ ሕብረተሰቡ ተገቢውን ጥንቃቄ እንዲያደርግም ነው ያሳሰቡት። የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ በአዋሽ፣ በአባይ፣ በባሮ አኮቦና ሌሎች ተፋሰሶች አካባቢ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግም ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል። በከተሞች አካባቢ የውኃ ማስወገጃ ሥርዓቶችን በአግባቡ መቆጣጠርና መከታተል አስፈላጊ መሆኑንም ጠቁመዋል። በክረምቱ ወቅት የሚኖረው ዝናብ በረባዳማና ሸለቋማ ሥፍራ የሚኖሩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ላይ ተፅዕኖ እንዳያሳድር ጥንቃቄ መደረግ አለበትም ብለዋል። በሌላ በኩል የአየር ሁኔታው ለግብርና እንቅስቃሴ ጉልህ ሚና ያለው በመሆኑ የሚኖረውን ዝናብ ምርታማነትን ለማሳደግ መጠቀም እንደሚገባም አቶ ፈጠነ አስገንዝበዋል። በክረምቱ የሚኖረው ዝናብ ግድቦች የውኃ እጥረት ሳያጋጥማቸው ኃይል እንዲያመነጩና ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ውጤታማነት አስተዋፅዖ ያለው መሆኑን ተናግረዋል።
የመከላከያ  ዋር ኮሌጅ  የአረንጓዴ  አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሄደ 
Jul 24, 2024 116
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2016(ኢዜአ)፦የመከላከያ ዋር ኮሌጅ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር አካሄደ። ኮሌጁ በመጪው ቅዳሜ የሚያካሂደውን የ2016 ዓ.ም የ2ኛ ባች መደበኛና አጭር ኮርስ ሰልጣኞች ምረቃ በዓል ምክንያት በማድረግ የተለያዩ መርሃ ግብሮችን እያካሄደ ነው፡፡ በዚህም ዛሬ በኮሌጁ ግቢ ውስጥ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የተካሄደ ሲሆን " ህይወቱን ለሚሰጥ ሰራዊት ደሜን በመለገስ ከጎኑ እቆማለሁ "በሚል መሪ ሃሳብም የደም ልገሳ ተካሂዷል፡፡   የመከላከያ ዋር ኮሌጅ ዋና አዛዥ ብርጋዴር ጄነራል ቡልቲ ታደሰ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ሰራዊቱ አገራዊ ግዳጆችን ከመወጣት ጎን ለጎን የአረንጓዴ አሻራ ተሳትፎውን አጠናክሮ ቀጥሏል ፡፡ ዛሬ በኮሌጁ የተካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የዚሁ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሩ ውጤታማ እንዲሆን የሚተከሉ ችግኞችን መንከባከብ እንደሚገባም አመልክተዋል፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን የመከላከያ ዋር ኮሌጅ ከየት ወዴት በሚል መሪ ሃሳብ የፓናል ውይይት እንደሚካሄድም ተገልጿል፡፡  
የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህን ጨምሮ የፓርቲው ጽሕፈት ቤት አመራሮችና ሠራተኞች አረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ
Jul 24, 2024 162
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 17/2016(ኢዜአ)፦ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህና የፓርቲው ዋና ፅህፈት ቤት ከፍተኛ አመራሮችና ሠራተኞች በለሚ ኩራ ክፍለ ከተማ የችግኝ ተከላ መርሐ-ግብር አካሂደዋል። አቶ አደም ፋራህ በመርሐ ግብሩ ላይ ባደረጉት ንግግር፥ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር የትናንት፣ የዛሬና የነገን ትውልድ የሚያስተሳስርና ኢትዮጵያ ምቹ ፕላኔት የመፍጠር ሚናዋን እየተወጣችበት የሚገኝ ግዙፍ ኢኒሼቲቭ መሆኑን ገልጸዋል።   ትላንት የተሰሩ ታሪኮችን ለማስቀጠል፣ አደጋዎችን በዘላቂነት ለመከላከል፣ መልክዓ ምድራችንን ከአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ ለመጠበቅ የሚያስችል ነው ብለዋል። ለዛሬው ትውልድ ለስራ ዕድል ፈጠራ፣ ምርታማነትን ለማሳደግና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና እየተጫወተ መሆኑንም ገልጸዋል። ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ለማሳካት ጉልህ አበርክቶ እንዳለውም አንስተዋል። ለነገው ትውልድ የምትመች ሀገርና ለመጪው የዓለም ትውልድ ምቹ ፕላኔትን ለማስተላለፍ ግዴታችንን እየተወጣን መሆኑን ማሳያ ነው ሲሉም ገልጸዋል። ለነገው ትውልድ የተሻለች ሀገርና ፕላኔት ለማስረከብ የጀመርነውን ጥረት የሚያሳካና ዓለም አቀፋዊ ሚናችንን እየተወጣን መሆኑን የተግባር ምስክር እንደሆነ አስረድተዋል። በመሆኑም በገጠርም ሆነ በከተማም ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ ገልጸዋል። ብልጽግና ፓርቲ ለመርሐ-ግብሩ መሳካት የመሪነት ሚናውን እየተወጣ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ፥ ኢትዮጵያን የለመለመች፣ ለነዋሪዎቿ ምቹ ለማድረግ ታሪኳን የሚመጥን ዘርፈ ብዙ ሥራ እየተሠራ ነው ብለዋል። አዲስ አበባ የዲፕሎማሲ ማዕከል በመሆኗ ስሟን የሚመጥን የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ እየተከናወነ ነው ሲሉ ገልጸዋል። አዲስ አበባን ውብና ምቹ ከተማ ለማድረግ መጠነ ሰፊ ሥራ እየተሠራ ሲሆን ለዚህ ዕውን መሆን ብልጽግና ፓርቲ ፖለቲካዊ ቁርጠኝነቱን በተግባር እያረጋገጠ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።   የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሐ-ግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) "የምትተክል ሀገር የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሀሳብ ሰኔ 22/2016 ዓ.ም በደቡብ ወሎ ዞን ሐይቅ ከተማ በይፋ ማስጀመራቸው ይታወቃል። በዚህ ዓመት 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኞችን በመትከል እስከ አሁን የተተከሉ ችግኞችን ብዛት 40 ቢሊዮን ለማድረስ ታቅዷል።
የባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አመራርና ሠራተኞች የአረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ
Jul 23, 2024 201
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አመራርና ሠራተኞች ከአጋር ተቋማት ጋር በመሆን የአረንጓዴ አሻራቸውን በሞጆ-ሀዋሳ የፍጥነት መንገድ ዳርቻ አኑረዋል። የዘንድሮው ሀገር አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር "የምትተክል ሀገር የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሃሳብ በመካሄድ ላይ ይገኛል። በዚሁ መርሃ-ግብር የተለያዩ ተቋማት አሻራቸውን እያኖሩ ሲሆን፤ በዛሬው ዕለትም የባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አመራርና ሠራተኞች ከሌሎች አጋር ተቋማት ጋር በመሆን በሞጆ-ሀዋሳ የፍጥነት መንገድ ዳርቻ አሻራቸውን አኑረዋል። የኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ዋና ስራ አስፈፃሚ በሪሶ አመሎ (ዶ/ር)፤ የተቋሙ አመራርና ሰራተኞች የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ላይ ያላቸውን ተሳትፎ አጠናክረው ቀጥለዋል ብለዋል።   ከዚህ በፊት በሞጆ ዙሪያ ጠዴ ቀበሌ የተራቆተ መሬት ላይ ችግኞችን በመትከልና በመንከባከብ ለአካባቢው ማስረከብ መቻሉን አስታውሰው አሁንም ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልፀዋል። በዘንድሮው ዓመትም ከ30 ሺህ በላይ ሀገር በቀል ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ ተግባራዊ እንቅስቃሴው ተጀምሯል ብለዋል። የድርጅቱ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ ወንድሙ ደንቡ፤ በተቋሙ ሰራተኞችና አጋር ተቋማት በሞጆ አከባቢ በርካታ ችግኞች እየተተከሉ አካባቢውም እየለማ መሆኑን ገልጸዋል።   ሌላኛው የተቋሙ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ ሲራጂ አብዱላ፤ በመርሃ ግብሩ ችግኞችን መትከል ብቻ ሳይሆን የመንከባከብ ስራው ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። በችግኝ ተከላው ተሳታፊ የሆኑ ሰራተኞችም በመርሃ ግብሩ ላይ በመሳተፋቸው መደሰታቸውን ገልጸው በቀጣይነትም ለመንከባከብ ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል። የድርጅቱ አመራርና ሰራተኞች አሻራቸውን ያኖሩት ከኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግ፣ ከፌደራል ፖሊስ፣ ከጉምሩክ ኮሚሽን እና ከክፍያ መንገዶች ኢንተርፕራይዝ ጋር በጋራ በመሆን ነው። በዘንድሮው ሀገር አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ መርኃግብር 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኞችን ለመትከል ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ መሆኑ ይታወቃል።    
የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት እና አስተዳደር ቢሮና የአዲስ አበባ ቤቶች ኮርፖሬሽን በጋራ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር አካሄዱ 
Jul 23, 2024 147
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ቤቶች ልማት እና አስተዳደር ቢሮና የአዲስ አበባ ቤቶች ኮርፖሬሽን አመራርና ሠራተኞች በጋራ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር ዛሬ አከናውነዋል። የአዲስ አበባ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ቅድስት ወልደጊዮርጊስ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቀልበስ ዋነኛው ሥራ ችግኞችን መትከል ነው። በዚህም ኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት በርካታ ችግኞችን መትከሏን ገልጸው፤ ቢሮውም የዚህ የመፍትሔ አካል ለመሆን የችግኝ ተከላዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በዘንድሮው ዓመት 40 ሺህ ችግኞችን ለመትከል መታቀዱንና በዛሬው ዕለትም 20 ሺህ ችግኞች መተከላቸውን አመላክተዋል። ቢሮው ቤት ከመገንባት ባሻገር በአረንጓዴ አሻራ፣ በአቅመ ደካሞች ቤት እድሳት፣ በማዕድ ማጋራትና በመሳሰሉት አሻራውን እያሳረፈ እንደሚገኝ ተናግረዋል። እንደ ሀገር ችግኞችን ለመትከል የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት የቤቶች ሴክተር የሚጠበቅበትን እንደሚወጣም አረጋግጠዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርኃ-ግብር ለትውልድ ከብክለት የጸዳ አገር የሚተላለፍበት መሆኑን ገልጸው፤ ችግኞችን በመትከልና በማጽደቅ ርብርብ ማድረግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።   የአዲስ አበባ ቤቶች ኮርፖሬሽን ዋና ዳይሬክተር ሽመልስ ታምራት በበኩላቸው፤ ችግኞችን መትከል ለመጪው ትውልድ አረንጓዴ አገርን ማስተላለፍ መሆኑን ገልፀዋል። የአረንጓዴ አሻራ-መርኃ ግብር የአረንጓዴ ልማት ሥራዎችን በጉልህ የሚያግዝ መሆኑንም አመላክተዋል።   የመርኃ-ግብሩ ተሳታፊዎችም የተከሏቸውን ችግኞች ለመንከባከብ ቁርጠኛ መሆናቸውን ገልፀዋል። ሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል በአረንጓዴ አሻራ-መርኃ ግብር በመሳተፍ ለስኬቱ ርብርብ እንዲያደርግም ጥሪ አቅርበዋል።  
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ትውልድ ተሻጋሪ አካባቢን ለማስረከብ  ትልቅ አስተዋጽኦ አለው 
Jul 23, 2024 132
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ትውልድ ተሻጋሪ አካባቢን ለማስረከብ ትልቅ አስተዋጽኦ አለው ሲሉ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሂክማ ኸይረዲን ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ ሥራ አስኪያጅ ጽህፈት ቤት ተጠሪ ተቋማቱን በማስተባበር በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር አካሂዷል። ዋና ሥራ አስኪያጇ ሂክማ ኸይረዲን በዚሁ ወቅት በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር እንደ ጽህፈት ቤት 40 ሺህ ችግኞች ለመትከል ማቀዳቸውን ገልፀዋል። ሥራ አስኪያጅ ጽህፈት ቤት እስከ ወረዳ ያሉ ተጠሪ ተቋማትን በማስተባበር በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ 10 ሺህ ችግኞችን በመትከል የአረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር አካሂደዋል። አረንጓዴ አሻራ ለከተማው ውበትን ከማጎናጸፉም በላይ የደን ሽፋንን በማሳደግ፤ በአየር ብክለት ምክንያት የሚደርሱ በርካታ ችግሮችን በመከላከል ረገድ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ አዲስ አበባን ለነዋሪዎቿ ምቹ ለእንግዶቿ ማራኪ እንድትሆን እየተሰራ መሆኑን ገልጸው፤ ለዚህም የአመራሩና የሠራተኛው ተሳትፎ ከፍተኛ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም አዲስ አበባን አረንጓዴ፣ ውብና ከአየር ብክለት የፀዳች ለማድረግ አጠቃላይ ማኅበረሰቡ የነቃ ተሳትፎውን በማድረግ ለትውልድ የሚሻገር ደማቅ አሻራውን የማኖር ሥራውን አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል፡፡   በመርሃ-ግብሩ ላይ ከተሳተፉት መካከል ወይዘሮ በየነች አንበሶ እና አቶ አደፍርስ አሰፋ እንደተናገሩት፤ ባለፉት ዓመታት በተካሄዱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሮች የተተከሉ ችግኞች ለከተማዋ ውበትን እያላበሱ በመሆኑ ተሳትፏቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል፡፡        
በትብብር ለዘላቂ ሰላም እየሰራን፤ ለትውልድ የሚሻገር አሻራችንን እያኖረን ነው - የማይጠብሪ ከተማ ነዋሪዎች
Jul 23, 2024 144
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦ በትብብር ለዘላቂ ሰላም ከመስራት በተጓዳኝ ለሀገር የሚበጅና ለትውልድ የሚሻገር የአረንጓዴ አሻራቸውን እያኖሩ መሆኑን የማይጠብሪ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። የማይጠብሪ ከተማና አካባቢው ነዋሪዎች በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኞችን በመትከል አሻራቸውን አኑረዋል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ከተሳተፉት መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች ሰላማችን ተመልሶ ወደ ልማት ስራዎች በመመለሳችን ተደስተናል ብለዋል። የሁሉን ነገር መሰረቱ ሰላም መሆኑን ያነሱት መቶ አለቃ አቢዮት መኮንን፤ ቀደም ሲል በአካባቢው የነበረው ጦርነት በብዙ መልኩ ጎትቶን ቆይቷል ብለዋል። አሁን ላይ ግን ሁሉም ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት በማረጋገጥ በተግባር በማሳየት በአብሮነት ለልማታችን እየሰራን ነው ሲሉ ተናግረዋል። በዛሬው እለትም በትብብር ለዘላቂ ሰላም ከመስራት በተጓዳኝ ለሀገር የሚበጅና ለትውልድ የሚሻገር የአረንጓዴ አሻራችንን አኑረናል ብለዋል። የከተማው የእንስሳት ኃብት የሥራ ሂደት አስተባባሪ ዶክተር ሞገስ አቦሃይ፤ የጦርነት ዳፋ ብዙ ዋጋ ያስከፈለ መሆኑን አስታውሰው አሁን ላይ በሙሉ አቅም ወደ ልማት በመገባቱ ሁሉም ደስተኛ መሆኑን ተናግረዋል። የከተማዋ ግብርና ጽህፈት ሰራተኛ የሆኑት ነኢማ መሀመድ ኑር፤ የአከባቢው ህዝብ በነቂስ ወጥቶ የተፋሰስ ልማት ሥራውን በስፋት ማካሄድ መቻሉን ገልጸዋል። የተተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ የግብርና እና ተያያዥ የልማት ተግባራትን ለማስቀጠል ሁሉም በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛው የከተማው ነዋሪ አቶ ሽፈራው ከበደ፤ በአረንጓዴ አሻራ በመሳተፋችን ደስታ ተሰምቶናል፤ ለቀጣዩ ትውልድ የታሪክ አሻራችንን የምናስቀምጥበት ዕድል ይፈጥራልም ብለዋል። የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በደቡብ ወሎ ዞን ሎጎ ሐይቅ ከተማ በይፋ ማስጀመራቸው ይታወሳል። በመርሃ ግብሩ 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ታቅዶ "የምትተክል ሀገር የሚያጸና ትውልድ" በሚል መሪ ኃሳብ በሀገር አቀፍ ደረጃ እነደቀጠለ ነው።      
የባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አመራርና ሠራተኞች የአረንጓዴ አሻራቸውን አኖሩ
Jul 23, 2024 97
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦ የባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አመራርና ሠራተኞች የአረንጓዴ አሻራቸውን በሞጆ-ሀዋሳ የፍጥነት መንገድ ዳርቻ አኖሩ። የዘንድሮው ሀገር አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር "የምትተክል ሀገር የሚያፀና ትውልድ" በሚል መሪ ሃሳብ በመካሄድ ላይ ነው። በዚሁ መርሃ-ግብር የተለያዩ ተቋማት አሻራቸውን እያኖሩ ሲሆን፤ በዛሬው ዕለትም የባህር ትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ አመራርና ሠራተኞች ከሌሎች አጋር ተቋማት ጋር በመሆን አሻራቸውን አኑረዋል። አመራርና ሰራተኞቹ የአረንጓዴ አሻራቸውን ያኖሩት በሞጆ-ሀዋሳ የፍጥነት መንገድ ዳርቻ ነው። ተቋሙ በዘንድሮው መርኃግብር ከ30ሺህ በላይ ሀገር በቀል ዛፎችን ጨምሮ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለመትከል አቅዶ እየሰራ መሆኑ ተገልጿል። የ2016 ዓ.ም ሀገር አቀፍ የአረንጓዴ አሻራ መርኃግብር 7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ ለመትከል ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ ነው።  
የአፍሪካ የውሃማ አካላት ሳምንት በአዲስ አበባ መካሄድ ጀመረ
Jul 23, 2024 125
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 16/2016(ኢዜአ)፦ በባህርና ውቅያኖስ ሀብቶች ላይ ግንዛቤ መፍጠር አላማው ያደረገ የአፍሪካ የውሃማ አካላት ሳምንት (ብሉ ኢኮኖሚ) ዛሬ በአፍሪካ ሕብረት ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ተጀምሯል። “የአፍሪካን የብሉ ኢኮኖሚ ሕዳሴ እውን ማድረግ” በሚል መሪ ቃል የሚከበረውን የአፍሪካ የውሃማ አካላት ሳምንት ያዘጋጁት የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን፣ የተባበሩት መንግስታት የልማት ፕሮግራም (ዩኤንዲፒ) እና አጋር አካላት ናቸው። የአፍሪካ የውሃማ አካላት ሳምንት የተመለከተ አውደ ጥናት በመካሄድ ላይ ይገኛል። በአውደ ጥናቱ ላይ የአፍሪካ ሕብረት የግብርና፣ገጠር ልማት፣ 'ብሉ ኢኮኖሚ' እና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽነር አምባሳደር ጆሴፋ ሳኮ፣ የኖርዌይ የዓለም አቀፍ ልማት ምክትል ሚኒስትር ቦርግ ሳንድካየር፣ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን አመራሮች፣ የሕብረቱ አባል ሀገራት ተወካዮች፣ የዘርፉ ተዋንያንና አጋር አካላት ተሳታፊ ሆነዋል። ሳምንቱ የባህርና ውቅያኖስ ሀብቶች ''ብሉ ኢኮኖሚ'' ፅንሰ ሀሳብ ላይ ሁሉን አቀፍ መረዳት መፍጠር እንዲሁም ያላቸውን ጠቀሜታዎችና ፈተናዎች የማስገንዘብ አላማ ያለው ነው። የተለያዩ የዘርፉ ባለድርሻ አካላትን በማስተባበር በብሉ ኢኮኖሚ ያሉ እድሎች ላይ በመምከር የጋራ እርምጃ መውሰድ የሚያስችል ትርጉም ያለው ትብብርን ማጠናከር የሚያስችል ምቹ መደላድልን ይፈጥራል ተብሏል። ፖሊሲ አውጪዎች በብሉ ኢኮኖሚ ላይ አዳዲስ የፖሊሲ ማዕቀፎችን ማዘጋጀትና በአፍሪካ የዘርፉን ኢኮኖሚ መደገፍ በሚችሉበት ሁኔታ ላይ ምክክርና የልምድ ልውውጥ እንደሚያደርጉ ተገልጿል። የአፍሪካ ሴቶችና ወጣቶች በብሉ ኢኮኖሚ ውስጥ ያላቸውን ተሳትፎ በማሳደግና በነሱ የሚመሩ የኢኮኖሚ ማዕቀፎችና የፈጠራ ሀሳቦችን መንደፍ ላይ ውይይት እንደሚደረግም ተመላክቷል። የብሉ ኢኮኖሚ አማራጮች ፣ ዓለም አቀፍ የውቅያኖስ ኢኮኖሚ፣ ቱሪዝም፣ የውሃ ሀብቶች ጥበቃና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት እንዲሁም ወጣቶችን ማብቃት ውይይት የሚደረግባቸው ርዕሰ ጉዳዮች እንደሆኑ ኢዜአ ከአፍሪካ ሕብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የአፍሪካ ውሃ አካላት ሳምንት እስከ ሐምሌ 18 ቀን 2016 ዓ.ም ይቆያል። የአፍሪካ የባህርና የውቅያኖስ ቀን ከነገ በስቲያ ይከበራል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም