አካባቢ ጥበቃ
በዘንድሮው ዓመት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 7 ነጥብ 3 ቢሊዮን ችግኞች ተዘጋጅተዋል
Apr 26, 2024 78
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- በዘንድሮው ዓመት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 7 ነጥብ 3 ቢሊዮን ችግኞች መዘጋጀታቸውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ብሔራዊ ዐቢይ ኮሚቴ ገለፀ። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ብሔራዊ ዐቢይ ኮሚቴ የችግኞችን የጽድቀት መጠንና የዘንድሮ ዓመት ዝግጅቶችን አስመልክቶ በኦሮሚያ ክልል የምስራቅ ሸዋ ዞን አዳኣ ወረዳ ጉብኝት አድርጓል። ከጉብኝቱ ቀጥሎ በቢሾፍቱ ከተማ የ2016/17 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ ዝግጅትና የቀጣይ የስራ አቅጣጫን አስመልክቶ የምክክር መድረክ አካሂዷል።   የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ብሔራዊ ዐቢይ ኮሚቴ ሰብሳቢ እና የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ(ዶ/ር)፤ ጉብኝቱ የተመዘገቡ ስኬቶችን በመገምገም የቀጣይ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ስኬት ለማጠናከር ነው ብለዋል። በ2015/16 ዓ.ም በጀት አመት በተካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን የደንና የፍራፍሬ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው ችግኞች መተከላቸውን አስታውሰዋል። በሁለት ዙር በተካሄደ የዳሰሳ ጥናትም የተተከሉ ችግኞችን በመንከባከብ የጽድቀት መጠናቸውን 90 ከመቶ ማድረስ እንደተቻለ አስታውቀዋል። ለዚህም በኦሮሚያ ምስራቅ ሸዋ ዞን አዳኣ ወረዳ በተደረገው የመስክ ምልከታ በተሰራ የአፈርና ውሃ ጥበቃ የችግኝ ተከላ ስራ ተራቁቶ የቆየን አካባቢ በደን መሸፈን መቻሉም አንዱ ማሳያ ነው ብለዋል። በአረንጓዴ አሻራ በለሙ የተፋሰስ ይዞታዎች ላይ በእንስሳት ማድለብና በንብ ማነብ መስኮች የሕብረተሰቡን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ ለማሳደግ መቻሉን ጠቅሰዋል። በ2016/17 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በዕቅድ ከተያዘው የ6 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ ውስጥ ከዕቅድ በላይ 7 ነጥብ 3 መዘጋጀቱን አስታውሰዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሚተከሉ ችግኞችም 1 ነጥብ 8 ሚሊየን ሄክታር መሬት ለተከላ ቦታ መዘጋጀቱን ገልጸዋል።   የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ብሔራዊ ዐቢይ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ እና የውሃና ኢነርርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ/ር)፥ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተራቆቱ አካባቢዎችን እንዲያገግሙ በማድረግ ለአፈርና ውሃ ጥበቃ ተጨባጭ ውጤት ማምጣቱን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩም በግብርና ምርታማነት በማሳደግ ለዜጎች በስራ ዕድል ፈጠራና በሥነ-ምግብ ስርዓት መሻሻል አዎንታዊ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም ቀጣይነት ያለው የውሃ ፍሰት በመፍጠር ለመስኖ ምርታማነት፣ ለግድቦች የውሃ ደህንነት እና ለንጹህ የምንጭ ውሃ ዕድገት ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል። የኦሮሚያ ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊ ኤሊያስ ከድር የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የዜጎችን ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ተጨባጭ ውጤት አስመዝግቧል ብለዋል። በዘንድሮው መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያሳድጉ የፍራፍሬ እና የደን ችግኞችን ለተከላ ዝግጁ ማድረግ እንደተቻለ ገልጸዋል። በመጪው ክረምት በሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዜጎች የነቃ ተሳትፎ በማድረግ ለአካባቢ ጥበቃና ለግብርና ምርታማነት አዎንታዊ ሚና መጫወት እንደሚኖርባቸውም በዚሁ ወቅት ተጠቅሷል።
በደቡብ ኢትዮጵያና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች በተያዘው ዓመት ከ713 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ይተከላሉ
Apr 26, 2024 84
ቦንጋና ዲላ፤ሚያዚያ 18/2016 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ከ713 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጎ ወደተግባር መገባቱ ተገለጸ። የየክልሎቹ ግብርና ቢሮዎች ከደን አካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ቁጥጥር ቢሮዎች ጋር በመተባበር የቅድመ ዝግጅት ሥራ እያከናወኑ መሆኑም ተመላክቷል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ ሀይለማሪያም ተስፋዬ ለኢዜአ እንዳሉት በክልሉ ከበልግ ወቅት ጀምሮ ከ372 ሚሊዮን በላይ የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ ይካሄዳል።   አስካሁንም ከአካባቢ ጥበቃ ጋር በመቀናጀት ችግኝ የማዘጋጀት ሥራ መጠናቀቁን ገልጸው የበልግ ወቅት የችግኝ ተከላ መርሀግብር ተከላ መጀመሩን አስረድተዋል። "ከሚተከሉት ችግኞች መካከል 32 ሚሊዮን ቡና እንዲሁም 27 ነጥብ 9 ሚሊዮኑ የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን የጠቆሙት አቶ ሃይለማርያም፣ ችግኞቹን በተያዘው የበልግ ወቅት ተክሎ ለማጠናቀቅ በርብርብ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ቀሪዎቹን ችግኞች በክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ መሆናቸውንም አመልክተዋል። በክልሉ በየዓመቱ የሚከናወኑ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራዎች የውሃ አቅምን በመጨመርና የመሬት ለምነትን በማጎልበት ለግብርና ልማቱ ውጤታማነት አስተዋጾ ማድረጋቸውን ሃላፊው ተናግረዋል። ህብረተሰቡም በችግኝ ተከላ ሲያደርገው የነበረውን ተሳትፎ በቀጣይም አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አስገንዝበዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ግብርና ቢሮ ምክትል ኃላፊና የተፈጥሮ ሀብት፣ መሬት አስተዳደርና አጠቃቀም ዘርፍ ኃላፊ አቶ ውብሸት ዘነበ በክልሉ ለአርንጓዴ ልማት ሥራ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው።   በተያዘው ዓመትም በአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብር ከ341 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ሲደረግ መቆየቱን ተናግረዋል። ከእዚህ ውስጥ ከ149 ሚሊዮን በላይ ችግኞች በተያዘው የበልግ ወቅት እንደሚተከሉ ጠቁመው፣ ቀሪ 192 ሚሊዮን ችግኞች በክረምት ወራት ይተከላሉ ብለዋል። ችግኞቹ ከክልሉ ደን፣ አካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ቁጥጥር ቢሮ ጋር በመተባበር መዘጋጀታቸውን የገለጹት ኃላፊው፣ የአረንጓዴ ልማት ሥራው በተቀናጀ መንገድ ይከናወናል ብለዋል። ባለፉት ዓመታት በህብረተሰቡ ተሳትፎ የተተከሉ ችግኞች የክልሉን የደን ሽፋን እያሳደጉት መሆኑንም ጠቅሰዋል። አቶ ውብሸት እንዳሉት የአረንጓዴ ልማት ሥራው የደን ሽፋኑን ከማሳደግ ባለፈ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚከናወኑ ሥራዎችን በእጅጉ እያገዘ ነው። በመሆኑም ህብረተሰቡ የተተከሉ ችግኞች እንዲጸድቁ ተገቢውን ጥበቃና ክብካቤ ማድረግ እንዳለበት አስገንዝበዋል። ባለው ዓመት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በክልሉ ከ288 ሚሊዮን በላይ ችግኞች የተተከሉ ሲሆን የጽድቀት መጠናቸውም 86 በመቶ መሆኑን የቢሮው መረጃ ያሳያል።    
የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የቆላማ ስርአተ ምህዳር የአየር ንብረት ለውጥ ማጣጣሚያ ፕሮጀክት እየተገበረ ነው
Apr 25, 2024 109
መቀሌ ፤ሚያዚያ 17/2016 (ኢዜአ)፦ በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች 120 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የቆላማ ስርአተ ምህዳር የአየር ንብረት ለውጥ ማጣጣሚያ ፕሮጀክት እየተገበረ መሆኑን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። ፕሮጀክቱን በትግራይ ክልል ለማስጀመር በተዘጋጀ የትውውቅ መድረክ ላይ እንደተመለከተው፣ ፕሮጀክቱ በቆላማ የሀገሪቱ አካባቢዎች 120 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው። በባለስልጣኑ የፕሮጀክቱ አስተባባሪ አቶ ደሳለኝ ሙሉጌታ እንደገለጹት የቆላማ ስርአተ ምህዳር የአየር ንብረት ለውጥ ማጣጣሚያ ፕሮጀክት በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች እየተተገበረ ይገኛል። በፕሮጀክቱም በዋነኛነት በከፍተኛ ሁኔታ እየተጎዳ ያለው የአካባቢ ስነምህዳር እንዲያገግም ለማድረግ የሚያግዙ ሥራዎች በመከናወን ላይ ናቸው። በተለይ በቆላማ አካባቢ ያሉ ነዋሪዎች የአፈር መከላትን ለመከላከል የደን ልማት ጥበቃ ሥራን ጨምሮ በተለያዩ የገቢ ማስገኛ የሥራ እድሎች እንዲሰማሩ መደረጉን ገልጸዋል። ከእዚህ በተጨማሪ ለአየር ንብረት ለውጥ መሻሻል የበኩላቸውን እንዲወጡ እየተደረገ መሆኑን ነው አቶ ደሳለኝ ያስረዱት። በዚህም ነዋሪዎች የአየር ንብረትን በማይጎዱ የልማት ሥራዎች እንዲሰማሩና እንደ ሶላር ያሉ የሃይል አማራጮችን የመጠቀም ባህላቸው እንዲጎለብት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። መንግስት ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም ጋር በመተባበር ካለፋት ሦስት ዓመታት ጀምሮ ፕሮጀክቱን እየተገበረ ይገኛል ያሉት አስተባባሪው፣ ፕሮጀክቱ በትግራይ ክልል በተለያዩ ምክንያቶች ሳይተገበር ቢቆይም አሁን ወደስራ እየገባ መሆኑን ገልጸዋል። ፕሮጀክቱን በሁለት የትግራይ ወረዳዎች በሚገኙ አራት የገጠር ቀበሌዎች ለመጀመሪያ ጊዜ ለማስጀመር መታቀዱንና የዛሬው መድረክም ፕሮጀክቱን ለማስተዋወቅ መዘጋጀቱን ተናግረዋል።   በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የአየር ንብረት ለውጥና የአካባቢ ባለስልጣን ሀላፊ አቶ ፀጋይ ገብረማሪያም በበኩላቸው እንዳሉት፣ ፕሮጀክቱ በትግራይ ዘግይቶ ቢጀመረም በህዝቡ የተደራጀ ተሳትፎ ለማሳካት ጠንክረን እንሰራልን በለዋል። ፕሮጀክቱን ለማስተዋወቅ በተዘጋጀ መድረክ ላይ ከሁለቱ ወረዳዎች እና ከሚመለከታቸው መስሪያ ቤቶች የተውጣጡ የሥራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል። የመድረኩ ተሳታፊዎችም ፕሮጀክቱን በተፋጠነ መልኩ ተግባራዊ በማድረግ የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትጋት እንደሚሰሩ ተናግረዋል።  
በኦሮሚያ ክልል ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር  እስካሁን 500 ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኝ ተዘጋጅቷል 
Apr 25, 2024 83
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 17/2016 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር እስካሁን 500 ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኝ መዘጋጀቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በኦሮሚያ ክልል አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ80 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፍጠሩም ተገልጿል። የቢሮው የደን ልማትና እንክብካቤ ዳይሬክተር ከተማ አብዲሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ በክልሉ የአረንጓዴ አሻራን ከተፋሰስ ልማትና ከሌማት ትሩፋት መርሐ ግብር ጋር በማቀናጀት እየተሰራ ነው። በክልሉ ባለፉት ዓመታት 18 ነጥብ 6 ቢሊዮን ችግኝ መተከሉን አስታውሰው የፅድቀት መጠን በአማካኝ ከ80 በመቶ በላይ መሆኑን ተናግረዋል። ክልሉ በመጪው ክረምት 5 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል አቅዶ እስካሁን 5 ነጥብ 4 ቢሊዮን ችግኝ ዝግጁ ማድረጉን ገልጸው ከዚህ ውስጥ 500 ሚሊዮኑ ለፍራፍሬ ምግብነት የሚውሉ ናቸው ብለዋል። ለደንና ሌሎችም አገልግሎቶች የሚውሉ ችግኞች መኖራቸውን ጠቅሰው፥ የችግኝ መትከያ ጉድጓዶችም ዝግጁ የማድረግ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሆነ ገልጸዋል። በአረጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን ከመከላከል ባለፈ ለዜጎች የስራ ዕድል እየተፈጠረ መሆኑን አስረድተዋል።   በዚህም ባለፉት ሁለት ዓመታት በቋሚነት ከ80 ሺህ በላይ ሚሆኑ ዜጎችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ዳይሬክተሩ ጠቁመዋል። የአረንጓዴ አሻራን ከተፋሰስ ልማትና ከሌማት ትሩፋት ጋር በማቀናጀት ዜጎች ችግኞችን በመንከባከብ ፍራፍሬ ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ እየሆኑ ነው ብለዋል። ወጣት ዲቢሳ ጋሹ እና ጥላሁን ደርሶ ከሌሎች ወጣቶች ጋር በማህበር በመደራጀት በአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የስራ እድል እንደተፈጠረላቸውና በሚያገኙት ገቢ ቤተሰባቸውን እያስተዳደሩ መሆኑን ገልጸዋል። በችግኝ ማፍላትና ሌሎችም ስራዎች በትጋት በመስራት ገቢያቸው እየጨመረ መምጣቱን ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት 5 ሚሊዮን ብር ካፒታል እንዳላቸው ገልጸዋል።    
ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከበቂ በላይ ችግኝ መዘጋጀቱን ተመልከተናል - የፌደራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን
Apr 25, 2024 87
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ከበቂ በላይ ችግኝ መዘጋጀቱን በመስክ ምልከታ ማረጋገጡን የፌደራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን ገለጸ። ግብርና ሚኒስቴር በበኩሉ መጪው ክረምት 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል የታቀደ ሲሆን በዝግጅት ደረጃ ከእቅድ በላይ 7 ቢሊዮን ችግኝ ዝግጁ መሆኑን ገልጿል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የበጀት ዓመቱን የመንግሥት የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ሲገመግሙ የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን ተቋቁሞ ትኩረት በተሰጣቸው ዘርፎች ላይ የመስክ ምልከታ እንዲያደርግ አቅጣጫ ማስቀመጣቸው ይታወሳል። በዚህም የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የሚያስተባብረው የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን የግብርና ሚኒስቴርን የመጪው ክረምት የአረጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ዝግጅትና በባለፈው ዓመት የተተከሉ ችግኞችንና የተፋሰስ ልማት ስራዎች ያሉበትን ደረጃ ተመልክቷል፡፡ በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ ፋኑሴ መኮንን፥ ኢትዮጵያ በአረጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ዜጎችን በማሳተፍ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ አበረታች ውጤት እያስመዘገበች ነው ብለዋል።   በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም በተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር እስካሁን 32 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኞች የተተከሉ ሲሆን በአማካይ ከ87 በመቶ በላይ መፅደቃቸውን ተናግረዋል። በመጪው ክረምት 6 ነጥብ 5 ቢሊዮን ችግኝ ለመትከል እቅድ የተያዘ ሲሆን በዝግጅት ደረጃ ከ7 ቢሊዮን በላይ ችግኝ ተዘጋጅቷል ነው ያሉት። ለተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል 60 በመቶ የሚሆኑት ለምግብነትና ለሌሎች አገልግሎቶች የሚውሉ ሲሆን 40 በመቶ ደግሞ ለደን ችግኝ የሚተከሉ እንደሆኑ ጠቁመዋል። የስፔስ ሳይንስና የጂኦ ስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተርና የሱፐርቪዥን ቡድኑ መሪ አቶ አብዲሳ ይልማ፥ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የአየር ንብረት ለውጥ ተፅኖን መቋቋምና የምግብ ዋስትናን መረጋገጥ እንደሚቻል ያሳየ ነው ብለዋል።   መርሐ ግብሩን ከአፈርና ውሃ ጥበቃ ጋር በማቀናጀት መተግበሩ የተራቆቱ አካባቢዎችና የደረቁ ምንጮች እንዲያገግሙ እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም እያስቻለ ነው ብለዋል። የሱፐርቪዥን ቡድኑ ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር በቂ ችግኝ የመትከያ ቦታ መዘጋጀቱን እንደተመለከተ ገልጸዋል። መርሐ ግብሩን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ችግኞችን በዝግጅት ወቅትና ከተተከሉ በኋላ ያሉበትን ደረጃ በቴክኖሎጂ በተደገፈ አሰራር መከታተልና መንከባከብ እንደሚገባ አሳስበዋል።
የኦሮሚያ ክልል ድርቅን በዘላቂነት መቋቋም የሚያስችሉ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን በትኩረት እያከናወነ መሆኑን ገለጸ
Apr 25, 2024 77
ቦረና፤ ሚያዝያ 17/2016(ኢዜአ)፡- የኦሮሚያ ክልል ድርቅን በዘላቂነት መቋቋም የሚያስችሉ የተለያዩ የልማት ሥራዎችን በትኩረት እያከናወነ መሆኑን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ ገለጹ። የተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች በቦረና ዞን ድርቅን በዘላቂነት ለመቋቋም እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል። ከጉብኝቱ በኋላ የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይሉ አዱኛ የክልሉ መንግስት ድርቅን በዘላቂነት ለመቋቋም የሚያስችሉ ሥራዎችን ትኩረት ሰጥቶ እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም በክልሉ ቆላማ አካባቢዎች በተደጋጋሚ ጊዜ የሚከሰተውን ድርቅ ለመቋቋም የአጭርና የረጅም ጊዜ ዕቅድ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። ከአጭር ጊዜ እቅድ መካከል ድርቅ በተደጋጋሚ በሚያጋጥማቸው አካባቢዎች የሚኖሩ ዜጎች በድርቅ ምክንያት ለከፋ ጉዳት እንዳይዳረጉ ተከታታይ ድጋፍ ማድረግ መሆኑን አንስተዋል። በዚህ ስራም በክልሉ የተወሰኑ ቦታዎች በተከሰተ ድርቅ ምክንያት በዜጎች ላይ የከፋ ጉዳት እንዳይደርስ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። ከረጅም ጊዜ ዕቅድ አንጻርም የህዝቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ እና የኢኮኖሚ እድገትን የሚያሳኩ ፕሮጀክቶች እየተተገበሩ መሆኑን አቶ ኃይሉ አስረድተዋል። እንደ እሳቸው ገለጻ በክልሉ እየተተገበሩ ከሚገኙ 73 ፕሮጀክቶች መካከል 36ቱ ድርቅ በሚያጠቃቸው ቆላማ አካባቢዎች የሚገኙ ናቸው። ፕሮጀክቶቹ በዋናነት አርብቶ አደሩን ወደ ከፊል አርሶ አደርነት የሚለውጡ የመስኖ መሰረተ ልማቶች፣ የመጠጥ ውሃ እና የመኖ ልማት መሆናቸውን ጠቅሰው፣ በቀጣይም ትላልቅ ፕሮጀክቶች እንደሚተገበሩ ገልጸዋል። የቦረና ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ በሪሶ ገኖ በበኩላቸው እንዳሉት በዞኑ ድርቅን በዘላቂነት ለመቋቋም የ18 አነስተኛ ግድቦች ግንባታ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል።   የአብዛኛዎቹ ግድቦች ግንባታ መጠናቀቁን የጠቆሙት አቶ በሪሶ፣ በተሰራው የበጋ መስኖ ልማት ስራም በሄክታር እስከ 75 ኩንታል በቆሎ መገኘቱንና የአትክልትና ፍራፍሬ ልማትም መከናወኑን ገልጸዋል። በእንስሳት መኖ ልማትም 75 ሺህ ቶን መኖ ተዘጋጅቶ መከማቸቱን ተናግረዋል። በጉብኝቱ ከተሳተፉት የመገናኛ ብዙኃን ኃላፊዎች መካከል የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ አድማሱ ዳምጠው እና የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ምክትል ሥራ አስፈጻሚ አቶ አብዱራህማን ሩቤ በበኩላቸው መገናኛ ብዙሃን የልማት ስራዎችን በተከታታይ መዘገብ አለባቸው ብለዋል። ችግሮች ሲከሰቱ ብቻ ከመዘገብ የዜጎችን ህይወት ለመቀየር የሚከናወኑ ሥራዎችንም ለህዝቡ ማሳወቅ እንደሚገባ ጠቅሰዋል።
የምግብ ዋስትናና የአየር ንብረት ለውጥን የተመለከተ አህጉራዊ የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው
Apr 23, 2024 120
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 15/2016(ኢዜአ)፦ የምግብ ዋስትናና የአየር ንብረት ለውጥ መከላከልን የተመለከተ አህጉራዊ የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ይገኛል። መድረኩ“ለአየር ንብረት ለውጥ ቴክኖሎጂ ተኮር መፍትሔዎች እና በአፍሪካ ለምግብ ዋስትና የማይበገር አቅም መገንባት፤ እድሎችና ፈተናዎች” በሚል መሪ ሀሳብ ነው እየተካሄደ የሚገኘው። 14ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ስምምነት ማዕቀፍ (UNFCCC) የአፍሪካ ፈራሚ አገራት ስብስባ (COP 14) በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ይገኛል። ከስብስባው ጎን ለጎን የአፍሪካ የምግብ ስርዓቶች እና የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችን የተመለከተ የምክክር መድረክ ነው። በመድረኩ ላይ የአፍሪካ ሪስክ ካፓሲቲ ዳይሬክተር ጀነራል ኢብራሂማ ቼክ ዲዮንግ፣ የአፍሪካ ሕብረት የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ “ብሉ ኢኮኖሚ” እና ዘላቂ ከባቢ አየር የስራ ክፍል አመራሮች፣ የግብርና ሚኒስትር ዶክተር ግርማ አመንቴ፣ የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ማንደፍሮ ለማና የመንግስት ከፍተኛ አመራሮች፣ የሌሎች የአፍሪካ አገራት የግብርናና የተፈጥሮ ሀብት ሚኒስትሮች፣ የልማት አጋሮችና የዘርፉ ተዋንያን ተገኝተዋል። የምክክር መድረኩን ያዘጋጁት የአፍሪካ ሕብረት ልዩ ተቋም የሆነው የአፍሪካ ሪስክ ካፒሲቲ(ARC)፣ከግብርና ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩትና የልማት አጋሮች ጋር በመተባበር ነው። በውይይቱ የአፍሪካ አገራት የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም፣ የምግብ ሉዓላዊነትን በመገንባት፣ የግብርና የገበያ ትስስርን ማጠናከር፣ የመሰረተ ልማት ችግሮችን ለመቅረፍና ዓለም ከደረሰበት ቴክኖሎጂ አኳያ የግብርና ቴክኖሎጂ ፈጠራ ስራዎችን እያከናወኗቸው ያሉ ተግባራትና በገጠሟቸው ፈተናዎች ላይ ምክክር እንደሚያደርጉ ተገልጿል። ስብስባው ትናንት በባለሙያዎች ደረጃ መካሄዱ ይታወቃል።  
ኢትዮጵያ በፈረንጆቹ 2025 ተጨማሪ የካርበን ሽያጭ ማግኘት የሚያስችላትን መስፈርት አሟልታለች - የኢትዮጵያ የደን ልማት
Apr 23, 2024 143
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በሚቀጥለው የፈረንጆቹ 2025 ተጨማሪ የካርበን ሽያጭ ገቢ ማግኘት የሚያስችላትን መስፈርት ማሟላቷን የኢትዮጵያ የደን ልማት አስታወቀ። ባለፉት አምስት አመታት ዜጎችን በማሳተፍ በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብሮች የደን ሽፋን እንዲጨምር ማድረግ ተችሏል፡፡ ከመርኃ ግብሩ ጎን ለጎን የደን ጭፍጨፋን ለመከላከል በተከናወኑ ተግባራት የደን ጭፍጨፋን በግማሽ መቀነስ መቻሉን ከተቋሙ የተገኘው መረጃ ያሳያል ። በኢትዮጵያ የደን ልማት የብሔራዊ ሬድ ፕላስ አስተባባሪ ዶክተር ይተብቱ ሞገስ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የተራቆቱ አካባቢዎችን በደን በመሸፈን የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም የራሷን ድርሻ እየተወጣች ነው። የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቋቋም ጉልህ ፋይዳ እያበረከተ ከሚገኘው የደን ልማት ከካርበን ሽያጭ ተጨማሪ የገቢ ምንጭ ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። የካርቦን ሽያጭ ገቢ ለማግኘት የተቀመጡ ዓለም አቀፍ መስፈርቶች እንዳሉ ጠቁመው ኢትዮጵያ ከካርቦን ሽያጭ ተጨማሪ ገቢ ማግኘት የሚያስችሏትን መስፈርቶች እንዳሟላች ተናግረዋል። የካርበን ሽያጭ ገቢ በማደግ ላይ ያሉ ሀገራት በአካባቢና በአየር ንብረት ሚዛናዊነት ጥበቃ ላይ የሚያበረክቱት የካርበን መጠን ተለክቶ የሚፈጸም የክፍያ ሥርዓት መሆኑን አስረድተዋል። በሰው ሰራሽ የደን ሽፋን የተራቆቱ አካባቢዎችን የማልማት ተግባሩ በባለሙያና በሳተላይት መረጃ ተንትኖ የሚቀርብ ሲሆን በዚህም ለአየር ንብረት ተጽዕኖና የካርበን ክምችት ያበረከተው አስተዋጽኦ ተለክቶ ለሽያጭ የሚቀርብ መሆኑን አንስተዋል። በኢትዮጵያ እየተሰራበት በሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የደን ሽፋኑን ከ17 በመቶ በላይ ማድረስ መቻሉ ሀገሪቷ ወሳኝ የአካባቢ ጥበቃ ምዕራፍ ላይ መሆኗን እንደሚሳይ ተናግረዋል። በዚህም ኢትዮጵያ በሚቀጥለው የፈረንጆቹ 2025 ከካርበን ሽያጭ ተጨማሪ ገቢ ማግኘት የሚያስችሉ ተግባራትን ማከናወኗን ገልጸዋል። የካርበን ሽያጭ ለመፈጸም የሚተከሉ ችግኞችን ደን በማድረግ፣ መረጃን በዲጂታልና በጂፒኤስ በመመዝገብ የተቀመጡ መስፈርቶችን አሟልቶ ማቅረብ እንደሚጠይቅ አንስተዋል። በኢትዮጵያ የተከናወኑ የደን ልማት ተግባራትን በአግባቡ አደራጅቶ በመመዝገብ ሪፖርት ቀርቦ ባለሙያዎች በአካልና በሳተላይት ምልከታ አድርገው ተጨማሪ የካርበን ሽያጭ ገቢ ማግኘት የሚያስችላትን መስፈርት ማሟላቷን የሚገልጽ ምላሸ እንደተሰጠ አስታውቀዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ የሚያስከትለውን ጫና ለመቀነስ የሚሰሩ አበረታች ተግባራትን አጠናክሮ ለማስቀጠል ከዓለም ባንክ፣ከኖርዌይና የአሜሪካ ኩባንያዎች ጋር በትብብር እየተሰራ እንደሆነም አስረድተዋል። ኢትዮጵያ እስካሁን ከካርበን ሽያጭ ከ100 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ ገቢ ማግኘቷን ጠቁመው፥ በሬድ ፕላስ በተደገፈው የባሌ ደን ካርበን ሽያጭ ብቻ በሁለት ዙር 12 ሚሊዮን ዩሮ ገቢ ተገኝቷል ብለዋል። ከካርበን ሽያጭ የሚገኘው ገቢ ለህብረተሰብ ተሳትፎና ለአካባቢ ጥበቃ ትኩረት በመስጠት ቀጣይነት ያለው የደን ጥበቃና እንክብካቤ ስራ እንደሚውል ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር ዘመቻን በማስቀጠል ከደን ልማት የካርበን ሽያጭ የሚገኘውን ገቢ ለማሳደግ የአካባቢ ጥበቃ ሙያተኞች የዜጎችን ተሳትፎ በማሳደግ ለደን ችግኝ ልማት ትኩረት እንዲሰጡ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የአካባቢ ጥበቃ እና ደን ልማት ስራ ዘላቂ ልማትን በማረጋገጥ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመቀነስ መሰረት በመሆኑ ቀጣይነት ያለው ስራ ማከናወን እንደሚገባም አስገንዝበዋል።  
በሲዳማ ክልል የፕላስቲክ ውጤቶች በአካባቢ ብክለት ላይ የሚያስከትሉትን ተጽዕኖ ለመከላከል ትኩረት ተሰጥቷል
Apr 23, 2024 205
ሐዋሳ፣ሚያዚያ 15/2016 (ኢዜአ)፡-በሲዳማ ክልል የፕላስቲክ ውጤቶች በአካባቢ ብክለት ላይ የሚያስከትሉትን ተጽዕኖ ለመከላከል ከማህበራት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ደንና አየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን አስታወቀ። የፕላሲቲክ ውጤቶችን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል የተደራጁ ማህበራት በበኩላቸው የአየር ብክለትን ለመከላከል እንደ ሀገር የተጀመረውን ንቅናቄ ውጤታማ ለማድረግ ተግተው እንደሚሰሩ ተናግረዋል። በባለስልጣኑ የአካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ዳይሬክተር አቶ ዮሴፍ ቲቦ ለኢዜአ እንደገለጹት"ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ" በሚል መሪ ቃል ክልል አቀፍ የንቅናቄ መድረክ በይፋ ተጀምሯል። በንቅናቄው ለስድስት ወራት የሚከናወኑ የዘመቻ ሥራዎች እንዳሉ ጠቁመው፣ስለአካባቢ ብክለት ከግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ ባለፈ ባለድርሻ አካለትን ንጹህና ጤናማ አካባቢን ለመፍጠር በትኩረት እንደሚሰራ አመልክተዋል። እንደ ሀገር የብክለት መነሻ ተብለው የተለዩ የፕላስቲክ፣ የአየር፣ የውሃ፣ የአፈርና የድምጽ ብክለቶች እንዳሉ አስታውሰው፣ ብክለት በአካባቢ ላይ የሚያስከትለውን ተጽዕኖ ከግምት ያስገባ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ትግበራ መገባቱን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም የፕላስቲክ ብክለት በአካባቢ ላይ የሚያስከትለውን ተጽዕኖ ለመከላከል ከተደራጁ ማህበራት ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ማህበራቱ በተለያዩ ከተሞች የፕላስቲክ ወጤቶችን ሰብስበው መልሶ ጥቅም ላይ መዋል በሚቻልበት ሥራ ላይ የተሰማሩ ሲሆን የንቅናቄው አካል እንዲሆኑም የግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራ መሰራቱን ገልጸዋል። ፕላስቲክ ከ500 እስከ 1000 ዓመት አፈር ውስጥ የመቆየት አቅም እንዳለው በጥናት መረጋገጡን የገለጹት ዳይሬክተሩ፣ በአካባቢ ብክለት ላይ ያለውን ተጽዕኖ ለመከላከል የህብተረተሰቡ ድርሻ የጎላ መሆኑን አስረድተዋል። በመሆኑም ህብረተሰቡ ፕላስቲክ ቆሻሻውን ለይቶ ለተደራጁ ማህበራት በመስጠት የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል የተጀመረውን ዘመቻ እንዲያግዝ ጥሪ አቅርበዋል:: የሃዋሳ ውበት ደረቅ ቆሻሻ ማስወገድና ሪሳይክሊንግ ሥራ ማህበር መስራችና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሄኖክ ዶንጋቶ በበኩላቸው ከ2010 ጀምሮ በተደራጀ መንገድ ቆሻሻን የመሰብሰብና ጥቅም ላይ የማዋል ስራ እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል።   ማህበሩ 86 ቋሚ እና ከ1ሺህ 500 በላይ ጊዜያዊ ሠራተኞች ያሉት ሲሆን በአምስት ተሽከርካሪዎች በመታገዝ ከየቤቱ ቆሻሻ የማሰባሰብ ሥራ ያከናውናል። ከሚሰበስቡት ቆሻሻ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ኮምፖስት ከማዘጋጀት በተጨማሪ ለአካባቢ ብክለት ተጽዕኖ ያላቸውን ፕላስቲክ ወጤቶች መልሶ ጥቅም ላይ እንዲውል የማድረግ ስራ እያከናወነ ይገኛል "ቆሻሻ ሃብት ነው" ያሉት አቶ ሄኖክ በዘፈቀደ የሚጣሉ የፕላስቲክ ምርቶችን በመሰብሰብ የሀዋሳን ሐይቅ እና አካባቢን ከብክለት ከመከላከል ባለፈ ለመልሶ ጥቅም በማዋል ገቢ ማግኘት እንደሚቻል ተናግረዋል። ፕላስቲክ በአካባቢ ላይ የሚያደርሰውን ተጽዕኖ ለመቀነስ ማህበሩ ከክልሉ አካባቢ ደንና አየር ንብረት ባለስልጣን ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በቀን ከ2ሺ 400 ኪሎ ግራም በላይ ፕላስቲክ እንደሚሰበስቡ የገለጹት ስራ አስኪያጁ ከሃዋሳ በተጨማሪ 11 በሚደርሱ የክልሉ ከተሞች፣ በሻሻመኔና ጥቁር ውሃ ኮፈሌና ሃላባ ከተሞች እንደሚሰበሰብ ተናግረዋል፡፡   በዚህም አንድ ኪሎ ፕላስቲክ ከ8እስከ 10 ብር እንደሚገዙ ገልጸው በዘርፉ የሚሰሩ ማህበራትን በማበራከት የአካባቢ ብክለትን መከላከልና ቆሻሻን ወደ ሃብት መቀየር ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ የኩል ፕላሲቲክ ሪሳይክልንግ ኢንተርፕራይዝ ማህበር አስተዳዳር ክፍል ሃላፊ ኢዮብ ኢያሱ ማህበሩ ለአካባቢ ብክለት ትልቅ ድርሻ ያላቸውን ፕላስቲኮች መልሶ የመጠቀም ስራ እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡   በፕላስቲክ ተረፈ ምርቶቹ በዋናነት ለችግኝ መትከያ የሚሆኑ "ፖሊ ባግ" እንደሚያመርቱ ገልጸው ፖሊ ባጎቹን በአረንጓዴ ልማት ለተሰማሩ ማህበራት እንደሚያስረክቡ ተናግረዋል፡፡ በዚህም ፕላስቲክ በአካባቢ ላይ የሚያሳድረውን ብክለት ለመቀነስ ከክልሉ ደንና የአየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን ጋር በቅንጅት እየሰራን ነው ብሏል፡፡ ከክልሉ ደንና የአየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው በወራት የተከፋፈሉ ስድስት ተግባራት የፕላስቲክ፣የአየር፣የውሃ፣የአፈርና የድምጽ ብክለትን ጨምሮ አካባቢና ማህበራዊ ተጽእኖ ግምገማ እስከ መጪው መስከረም የሚከናወኑ ተግባራት ናቸው፡፡  
በክልሉ የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል የተቀናጀ እንቅስቃሴ ማድረግ እንደሚጠበቅ ተገለጸ
Apr 22, 2024 154
ባህር ዳር ፤ ሚያዚያ 14/2016 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በየደረጃው የሚገኙ የአመራር አባላትና ባለሙያዎች የአካባቢ ብክለት ለመከላከል የተቀናጀ እንቅስቃሴ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ አሳሰቡ። ‘‘ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ!’’ በሚል መሪ ሃሳብ የአካባቢ ጥበቃና ብክለትን የመከላከል ዘመቻ የንቅናቄ ማስጀመሪያ መድረክ ዛሬ በባህር ዳር ተካሂዷል።   ርዕሰ መስተዳደሩ አቶ አረጋ ከበደ እንደገለጹት፤ በአየር ንብረት ለውጥ መባባስ በየጊዜው እየተስተዋለ ያለው ድርቅ፣ ጎርፍና ረሃብ ለዜጎች ፈተና እየሆነ መጥቷል። ለዚህም የአካባቢ ብክለትን በዘላቂነት ለመከላከል መንግሥት ለአረንጓዴ ልማት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እያከናወነ ያለው ሥራ ውጤት እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም የአየር ንብረት ለውጥ እያስከተለ ያለውን ብክለት በዘላቂነት ለመከላከል በየተቋማቱ የሚገኙ አመራር አባላትና ባለሙያዎች ተገንዝበው የተቀናጀ ርብርብ እንዲያደርጉ አስገንዝበዋል። በተለይም በትላልቅ ከተሞች የብክለት ምንጭ የሆኑና በየቦታው የሚጣሉ የፕላስቲክ ውጤቶች ለገቢ ማስገኛና ለኑሮ ማሻሻያ እንዲውሉ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል። የክልሉ የአካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋሁን አለምነህ በበኩላቸው፤ በከተሞች የሚስተዋለው የአካባቢ ብክለት ለማስወገድ የሁሉንም አካላት ቅንጅታዊ ርብርብ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።   በተለይ በየቦታው የሚጣሉ ፕላስቲኮችን በቀላሉ መከላከል ካልተቻለ ኅብረተሰቡን ለከፋ የጤና ችግሮች ከማጋለጡም በላይ፤ የከተሞች ውበትና ደህንነት ችግር ላይ እንዲወድቅ ያደርጋል። ለዚህም ለቀጣይ ስድስት ወራት የሚካሄደው የአካባቢ ጥበቃ የግንዛቤ ፈጠራና የህዝብ ንቅናቄ ዘመቻ ከዚህ በፊት የተገኙ ውጤቶችን አጠናክሮ ለማስቀጠል የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም ክልሉ ከአካባቢ ብክለት ነፃ፣ ምቹና ለሰው ልጆች መኖሪያ ተስማሚ እንዲሆን ባለድርሻ አካላት ድርሻቸውን እንዲወጡም ዋና ዳይሬክተሩ ጥሪ አቅርበዋል። ''በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት እየተራቆተ የሚገኘውን የተፈጥሮ ሃብት መልሶ ለመተካት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እየተተገበረ ይገኛል'' ያሉት ደግሞ የፌዴራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሴ ለማ ናቸው።   በከተሞች አካባቢ የሚስተዋለውን የፕላስቲክ ቆሻሻን ለመከላከል የተለያዩ የህዝብ ንቅናቄ ስራዎችን ማገዝና ውጤቱን ለማፅናት ትኩረት የተሰጠው ሀገራዊ ተግባር መሆኑን አመልክተዋል። ወጣት አይቸው ደባስ በበኩሉ፤ የወዳደቁ ፕላስቲኮችን ሰብስቦና ፈጭቶ ለተለያዩ ፋብሪካዎች እያቀረበ መሆኑን ገልጿል።   በወር ውስጥም እስከ 40 ሺህ ኪሎ ግራም የወዳደቁ ፕላስቲኮችን በመፍጨትና በመጨፍለቅ ለፋብሪካዎች ግብዓት እንዲሆኑ በማቅረብ ላይ እንደሚገኝ ተናግሯል። በመድረኩ የክልል፣ የፌዴራልና የዞን የስራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳታፊ ሆነዋል።
የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ያረጁ የቡና ተክሎችን በአዲስ ለመተካት ወደተግባር ተገብቷል
Apr 22, 2024 155
ዲላ ፤ሚያዝያ 14/2016 (ኢዜአ)፦የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ያረጁ የቡና ተክሎችን በአዲስ ለመተካት ወደተግባር መገባቱ ተገለጸ። በቡና ምርትና ምርታማነት ላይ ተሞክሮን ለመለዋወጥ ያለመ የመስክ ምልከታ በጌዴኦ ዞን ዲላ ዙሪያ ወረዳ ተካሂዷል። በመስክ ምልከታው ላይ የተሳተፉት የደቡብ ኢትዮጵያ፣ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች፣ የአማራና የጋምቤላ ክልሎች የዘርፉ አመራሮች እንደገለጹት፣ በየክልላቸው የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሰራ ነው። በዚህም በተያዘው የሚያዚያ ወር ከ96 ሚሊዮን 700 ሺህ በላይ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች ተከላ ሥራ እየተከናወነ መሆኑም ተናግረዋል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቡናና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን የቡና ልማት ዘርፍ ሃላፊ አቶ አማኑኤል ብሩ ለኢዜአ እንደገለጹት በክልሉ በ221 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ቡና ይለማል። የቡና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ዘንድሮ ያረጁ የቡና ተክሎችን በመተካትና አዲስ የቡና ማሳ በማስፋት ከ8ሺህ 800 ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ ቡና ለማልማት ታቅዶ እየተሰራ ነው ብለዋል። ለተከላ ከተዘጋጁ 35 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞች ውስጥ 32 ሚሊዮኑ በተያዘው ሚያዚያ ወር ተከላቸው እንደሚከናወን ተናግረዋል።   ክልሉ ለቡና ልማት ያለውን ያልተነካ አቅም በሚገባ ለመጠቀም በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የአማራ ክልል ግብርና ቢሮ የሆርቲካልቸርና መስኖ አጠቃቀም ቡድን መሪ አቶ ተሻለ አይናለም ናቸው። እንደ ቡድን መሪው ገለጻ ከዓመታዊ ሰብሎች በተጓዳኝ የቡናና ቅመማ ቅመም ምርቶች ያላቸውን ሀገራዊ ፋይዳ በመረዳት በልዩ ትኩረት እየተሰራ ነው። ባለፉት ዓመታት በየዓመቱ በአማካይ ከ7 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመትከል በክልሉ በቡና የተሸፈነ መሬት ከ28ሺህ 300 ሄክታር በላይ ለማድረስ ተችሏል። ዘንድሮም በ12 የችግኝ ጣቢያዎች ከዘጠኝ ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኞች መዘጋጀታቸውን ጠቁመው፣ በተያዘው ሚያዚያ ወር 7 ሚሊዮን 700 ሺህ ችግኝ ይተከላል ብለዋል።   የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ አስራት መኩሪያ በበኩላቸው እንደገለጹት በክልሉ 560ሺህ ሄክታር ላይ ቡና በተለያዩ መንገዶች እየለማ ይገኛል። በእዚህም ክልሉ በቡና ምርት አቅርቦትና በወጪ ንግድ ቀዳሚ መሆኑን አንስተው፣ በተያዘው ዓመት ከ59 ሺህ ኪሎ ግራም በላይ የዘር ቡና በክልሉ በማዘጋጀት ከራሱ ባለፈ ለአጎራባች ክልሎች ጭምር የዘር ምንጭ ሆኖ እያገለገለ መሆኑን ገልጸዋል። በቡና እደሳት በተለይ ያረጀ የቡና ተክልን ነቅሎ በተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች የመተካቱ ሥራ ትኩረት ተሰጥቶታል ያሉት አቶ አስራት፣ በተያዘው ዓመት ከ3ሺህ ሄክታር በሚበልጥ ማሳ ላይ የቡና እድሳት ሥራ መከናወኑን ተናግረዋል። በታደሰና በአዲስ መሬት በክልሉ ከ70 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች ዘንድሮ እንደሚተከሉና 42 ሚሊዮኑ በተያዘው ወር ተከላቸው የሚከናወን መሆኑን አስረድተዋል።   በጋምቤላ ክልል የእርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ የቡናና ሻይ ቅመማ ቅመም ምርት ጥራት ዳይሬክተር አቶ እሸቱ ዘውዴ በበኩላቸው በክልሉ ሦስት ወረዳዎች በ61 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ቡና በአርሶ አደሮችና በአልሚ ባለሀብቶች እንደሚመረት ተናግረዋል። ይሁንና በአንዱ ወረዳ ከሚገኘው የቡና ተክል ከ70 በመቶ በላይ የሚሆነው በእርጅና ምክንያት ከምርት ውጭ በመሆኑ የእድሳት ሥራው በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። "በተያዘው ዓመት ከ15 ሚሊዮን በላይ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ለመትከል እየተሰራ ነው" ያሉት አቶ እሸቱ፣ ይህም በክልሉ በሄክታር የሚገኘውን 6 ነጥብ 6 ኩንታል አማካኝ ምርት ወደ 9 ኩንታል ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት እንደሚያግዝ ተናግረወዋል። በመስክ ምልከታው ላይ ቡና ከሚለማባቸው የአገሪቱ ክልሎች የተወጣጡ የዘርፉ ሥራ ሃላፊዎችና አርሶ አደሮች የተሳተፉበት የመስክ ምልከታ በጌዴኦ ዞን ዲላ ዙሪያ ወረዳ መካሄዱ የሚታወስ ነው።      
አካባቢን መንከባከብና የተፈጥሮ ውበትን  ማቆየት የሁሉም ባለድርሻ አካላት ሃላፊነት ነው
Apr 22, 2024 125
ሠመራ፤ ሚያዝያ 14/2016 (ኢዜአ)፦ አካባቢን መንከባከብና የተፈጥሮን ውበት ማቆየት የሁሉም ባለድርሻ አካላት ሃላፊነት መሆኑን በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአፋር ክልል ኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ አቶ ዓሊ መሐመድ ተናገሩ። "ብክለት ይብቃ-ውበት ይንቃ" በሚል መሪ ሐሳብ የተጀመረው አገር አቀፍ የአካባቢ ብክለትን የማስወገድ ንቅናቄ በአፋር ክልል ደረጃ የማስጀመሪያ መርሐ-ግብር ዛሬ በሠመራ በመካሄድ ላይ ይገኛል። በመድረኩ ላይ የተገኙት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአፋር ክልል ኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ አቶ ዓሊ መሐመድ እንዳሉት አካባቢን መጠበቅ በተለይም የሰው ልጆችን አኗኗር በበጎ ሁኔታ መያዝና ደህንነቱን መጠበቅ ነው። ዜጎች በንፁህና ጤናማ አካባቢ የመኖር መብታቸው እንዲከበር የክልሉ መንግስት በርካታ ጥረቶችን በማከናወን ላይ እንደሚገኝ አቶ ዓሊ አስረድተዋል። የአካባቢ ብክለት በዓለማችን በሰውና በእንስሳት ጤና ላይ ከቀላል እስከ ከባድ ጉዳት በማድረስ ላይ ይገኛል ያሉት አቶ ዓሊ፤ የአካባቢ ጥበቃና እንክብካቤ ስራዎች ለአንድ አካል ብቻ የሚተው ሳይሆን የተቀናጀ ተሳትፎ የሚያሻው መሆኑን ተናግረዋል። የአካባቢን ፅዳትና ውበት ችላ ማለት የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከማዛባቱም ባሻገር የከተሞቻችንን ብሎም የሐገራችንን ገፅታ በእጅጉ ያጎድፋል ብለዋል። በመሆኑም በሁሉም የልማት ዘርፎች ላይ የጀመርናቸው የነቃ ተሳትፎን በማጠናከር አካባቢያችንን አረንጓዴ ውብና ሳቢ ማድረግ ያሻል ብለዋል። የክልሉ አካባቢ ጥበቃ፣ ገጠር መሬት አጠቃቀምና አስተዳደር ቢሮ ሃላፊ አቶ አህመድ ኢብራሂም በበኩላቸው በክልሉ ያሉት አደረጃጀቶች እየሰፉና ከተሞች እያደጉ መምጣታቸው ትኩረት የሚሻ ጉዳይ ነው ብለዋል። በተለይም የፕላስቲክ ብክለትን ለማስወገድ በቀዳሚነት የአመራሩ ሚና ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የተገኙት የኢፌዴሪ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬነሽ መኩሪያ እንዳሉት የኘላስቲክ፣ የአየር፣ የውሃ፣ የአፈርና የድምፅ ብክለቶቾ በአካባቢ ብክለት ውስጥ የሚካተቱ ናቸው። ይህ የንቅናቄ መርሐ ግብር ብክለትን የሚያስከትሉ መንስዔዎች ላይ ግንዛቤን ለማሳደግ ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። የአካባቢ ብክለት በከፍተኛ ደረጃ የጤና ጠንቅ እያስከተለ በመሆኑ በተለይሞ የኘላስቲክ ብክለት ለመቀነስ ንቅናቄው አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል። በንቅናቄ መድረኩ የፌዴራልና የክልሉ ከፍተኛ የአመራር አካላት ተገኝተዋል።  
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የሚኖረው የዝናብ ሁኔታ ለበልግ አብቃይ አካባቢዎች አመቺ ነው
Apr 22, 2024 125
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2016 (ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የሚኖረው የዝናብ ሁኔታ ቀደም ብለው ለተዘሩ የበልግ ሰብሎች እንዲሁም ቋሚ ተክሎች አመቺ ሁኔታ እንደሚፈጥር የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ በቀጣዩቹ አስር ቀናት በደቡብ፣ በምስራቅ፣ በሰሜን ምስራቅና በመካከለኛው የአገሪቱ አካባቢዎች ከቀላል እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚኖራቸው አመልክቷል። በመሆኑም የሚጠበቀው እርጥበት ቀደም ብለው ለተዘሩ የበልግ ሰብሎችና ለቋሚ ተክሎች የውሃ ፍላጎት ለሟሟላት እንዲሁም የመኸር ሰብሎችን ወቅቱን በጠበቀ ሁኔታ ለመዝራት ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል። አርሷአደሩ የሚገኘውን እርጥበት ለመጠቀም የሚያስችል አስፈላጊውን የግብዓት ዝግጅት ማድረግ እንደሚጠበቅበትም ተመላክቷል። የሚጠበቀው እርጥበት ለእንስሳት መኖና ለመጠጥ ውሃ አቅርቦት ከፍተኛ ሚና ስለሚኖረው በመደበኛ ሁኔታ ውሃ አጠር የሆኑ አካባቢዎችን በማሳም ሆነ ከማሳ ውጪ የውሃ እቀባ ስራዎችን በተገቢው ማከናወን ይገባቸዋል ። በሌላ በኩል በሰሜን ምስራቅ፣ በምስራቅና በደቡብ ምስራቅ የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ ከፍተኛ መጠን ያለው እርጥበት እንደሚጠበቅም የሚቲዎሮሎጂ ትንበያው ያመላክታል። ይህ ሁኔታ በተወሰኑ ውሃ ገብ በሆኑና በወንዝ ዳርቻ ባሉ ማሳዎች ላይ የውሃ መተኛትና የአፈር መታጠብን ሊያስከትል ስለሚችል ከወዲሁ ጥንቃቄ ሊደረግ እንደሚገባም መግለጫው አሳስቧል። ከቅድመ ጥንቃቄ ስራዎች ጎን ለጎን የሚገኘውን እርጥበት በላቀ ሁኔታ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚያስችሉ ስራዎችን ማከናወን እንደሚገባም ተገልጿል። በተጨማሪም በቀጣዮቹ አስር ቀናት በአፋር ደናክል፣አዋሽ ስምጥ ሸለቆ፣ገናሌዳዋ እና ዋቤ ሸበሌ ተፋሰሶች ላይ ከፍተኛ መጠን ያለው እርጥበት የሚኖር ሲሆን በሌሎች ተፋሰሶች ላይ ደግሞ ከመጠነኛ እስከ መካከለኛ መጠን ያለው እርጥበት ይኖራቸዋል። ይህ ሁኔታ በየተፋሰሶች የሚገኙት የውሃ አካላት የተሻለ የውሃ መጠን እንዲኖራቸው ከማድረግ አንጻር አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል። ለመስኖም ሆነ ለሃይል ማመንጨት የሚያገለግሉ የግድቦችን የውሃ መጠን የሚያሻሻል በመሆኑ ይህንኑ እድል ለመጠቀም የሚያስችል የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን ተግባራዊ ማድረግ ያስፈልጋልም ተብሏል።    
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የቡና ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርኃ ግብር እየተካሄደ ነው
Apr 22, 2024 182
ዲላ፤ ሚያዝያ 14/2016 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የተሻሻሉ የቡና ችግኝ ተከላ ማስጀመሪያ መርኃ ግብር በጌዴኦ ዞን ዲላ ዙያ ወረዳ ጎላ ቀበሌ እየተካሄደ ነው። የክልሉ ቡናና ቅመማ ቅመም ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ አማኑኤል ብሩ ለኢዜአ እንዳሉት ክልላዊ የቡና ችግኝ ተከላ መርኃ ግብር እየተሄደ ነው። በክልሉ ከአንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ቶን በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያን ለቡናው ችግኝ ተከላ ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል። በተያዘው ዓመት ከ35 ሚሊዬን በላይ የተሻሻሉ የቡና ችግኞች በክልሉ ለተከላ መዘጋጀታቸውን ጠቅሰው፤ ከ32 ሚሊዬን የሚልቀው በተያዘው ሚያዝያ ወር የሚተከል መሆኑን ተናግረዋል።   በክልሉ ያረጁ የቡና ተክሎችን በተሻሻሉ ዝሪያዎች መተካትን ጨምሮ የተለያዩ የምርታማነት ማሻሻያ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህም በሄክታር ሰባት ነጥብ አራት ኩንታል የሆነውን የክልሉን አማካይ የቡና ምርታማነት በቀጣይ ዓመት ወደ ዘጠኝ ኩንታል ለማሳደግ ግብ ተጥሎ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተከላው ማስጀመሪያ መርሃ ግብር የክልሉ አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፀሐይ ወራሳን ጨምሮ ሌሎች የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት እንዲሁም አርሶ አደሮች ተሳታፊ ሆነዋል።    
​​​​​​​በናይል ተፋስስ የድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተፋሰሱ ሀገራት ትብብር ወሳኝ ነው- የናይል ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ 
Apr 22, 2024 77
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2016 (ኢዜአ)፦ በናይል ተፋስስ የድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን ዘላቂነት እና ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተፋሰሱ ሀገራት ትብብር ወሳኝ መሆኑን የናይል ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ ገለጸ። የናይል ተፋስስ ኢኒሼቲቭ ከባለድርሻ አካላት ጋር በአዲስ አበባ የምክክር መድረክ እያካሄደ ነው። የናይል ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ ዋና ዳይሬክተር ፍሎሬንስ አዶንጎ (ዶ/ር) እንዳሉት፥ ኢትዮጵያን ጨምሮ 11 ሀገራትን ያቀፈው ኢኒሼቲቩ የተፋሰሱን ፀጋዎች በጋራ በማልማት ማህበረ ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና ተጠቃሚነትን የማረጋገጥ ዓላማ አለው። 25 ዓመታትን ያስቆጠረው የናይል ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ ድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን በትብብር ማልማት፣ የውሃ ሀብት ስራ አመራር እና የውሃ ሀብቶች ልማት ተጠቃሚነት ላይ ያተኮረ መሆኑን ገልፀዋል። በቀጣናው ፈተናዎችን በመሻገር የድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን ፍትሐዊ አጠቃቀም እና የውሃ ሀብት ዘላቂነትን ለማረጋገጥ የተፋሰሱ ሀገራት ትብብርና ቁርጠኝነት ወሳኝ ነው ብለዋል። ለዚህም የሀገራቱን የጋራ ህልም፣ አንድነትና የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በጋራ መስራት እንደሚገባ ጠቅሰው፥ ስትራቴጂካዊ ፕሮግራሞችን ገቢራዊ ማድረግ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል። ኢኒሼቲቩ በአቅም ግንባታ እና ምክክር ላይ እየሰራ ሲሆን የተፋሰሱን ህዝብ ኑሮ የሚያሻሽሉ ዉሃ ነክ ኢንቨስትመንት እንዲስፋፋ እየሰራ ነው ብለዋል። በሰላምና ደህንነት፣ በውሃ ዋስትና፣ በኃይል፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በምግብ ዋስትና ያሉ ፈተናዎችን ለመሻገር እንደ ሀገርና እንደ ተፋሰስ በትብብር መስራት ይገባል ነው ያሉት። ከሌሎች ቀጣናዊ ድርጅቶች ጋር በመተባበር ሰላምና ልማት እንዲረጋገጥ፣ ስራ ፈጠራና ድህነት ቅነሳ ስራዎች ላይ በትኩረት እንደሚሰራ ጠቁመዋል። የናይል ተፋሰስ ኢንሼቲቭን ወደ ናይል ተፋሰስ ኮሚሽን ቀጣናዊ ተቋም ለማሸጋገር የተደረሰውን የሕግ ማዕቀፍ ያልፈረሙ አባል ሀገራት እንዲፈርሙም ጥሪ አቅርበዋል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር አብርሃም አዱኛ በበኩላቸው፤ ኢኒሼቲቩ በፈተናዎች ውስጥም ሆኖ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን ጠቅሰዋል። የጋራ ፕሮጀክቶች እንዲተገበሩ በማድረግ ለሀገራዊና ቀጣናዊ ስራዎች ጉል አበርክቶ እንዳለው ጠቅሰው፣ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የሀገራቱን የጋራ ግብ ዕውን ለማድረግ እየሰራ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በኃይል ዘርፍ ከጎረቤት ሀገራት ጋር እየተሳሰረች መሆኑን ገልፀው፣ በድንበር ተሻጋሪ ወንዞች ላይ የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያረጋግጡ ፕሮጀክቶች ለመተግበር ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ የምትገነባቸው ግድቦች ከራሷ አልፎ ለታችኛው ተፋሰስ ሀገራት ጎርፍና ሌሎች አደጋዎችን በመቀነስ ረገድ ያላቸውን ወሳኝ አስተዋፅኦ አንስተዋል። ኢትዮጵያ በተፋሰሱ ሀገራት ፍትሐዊና የጋራ ተጠቃሚነት ዕውን እንዲሆን አበክራ እንደምትሰራም አረጋግጠዋል። የሀገራቱ የጋራ አደረጃጅት የሆነው የናይል ተፋሰስ ኢኒሼቲቭ ወደ ሕጋዊ ቀጣናዊ ኮሚሽን እንዲሸጋገር ያላትን ፅኑ መሻት ገልፀው፣ ሀገራቱም ስምምነቱን ማፅደቅ እንዳለባቸው ገልጸዋል።    
በክልሉ የአካባቢ ብክለትን በማስወገድ ምቹ ስነ-ምህዳር ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ህብረተሰቡ የድርሻውን እንዲወጣ ተጠየቀ 
Apr 22, 2024 163
ባህር ዳር ፤ ሚያዚያ 14/2016 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የአካባቢ ብክለትን በዘላቂነት በማስወገድ ለሰዎች ተስማሚ ስነ-ምህዳር ለመፍጠር በሚደረገው ሁሉን አቀፍ ጥረት ህብረተሰብ የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሳሰቡ። "ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ" በሚል መሪ ሀሳብ ብክለትን መከላከልና አካባቢ ጥበቃ ላይ ያተኮረ ክልል አቀፍ የንቅናቄ መድረክ በባህር ዳር ከተማ መካሄድ ጀምሯል። ርዕሰ መስተዳድሩ አቶ አረጋ ከበደ እንደገለጹት፤ አካባቢን ከብክለት በመጠበቅ ለሰው ልጅ ተስማሚ የሆነ ስነ ምህዳር ለመፍጠር በተቀናጀ መንገድ መስራት ይገባል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ከሚያዚያ ወር 2016 እስከ መስከረም 2017 ዓ.ም በሚካሄደው የአካባቢ ጥበቃ ልዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ ንቅናቄ በህብረተሰቡ ዘንድ ስለአካባቢ ጥበቃ በቂ ግንዛቤ መፍጠር እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በየአካባቢው በዘፈቀደ የሚጣሉ ፕላስቲኮችን ዘወትር በማፅዳት አካባቢን ከብክለት ነፃ የማድረግና ስነ-ምህዳርን በዘላቂነት የመጠበቅ ሥራ የሁሉም ህብረተሰብ ኃላፊነት መሆን እንዳለበትም አሳስበዋል። በየደረጃው ያለው አመራርና ባለሙያም ብክለት እያስከተለ ያለውን አደጋ በዘላቂነት ለመከላከል ለህብረተሰቡ ሰፊ ግንዛቤ በመፍጠር በትኩረት ሊሰራ ይገባል ሲሉም ገልጸዋል። በከተሞች የሚስተዋለውን የፕላስትክ ቆሻሻ የማስወገድ ብቻ ሳይሆን መልሶ ጥቅም ላይ የሚውልበት መንገድ እንዲፈጠር በትኩረት እንደሚሰራ አቶ አረጋ አመልክተዋል ''ብክለት የአካባቢን ስነ-ምህዳር ከመጉዳት ባለፈ ህይወት ላላቸው አካላት የሞት መንስኤ ነው'' ያሉት ደግም የክልሉ የአካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋሁን አለምነህ ናቸው። ከብክለት ነፃና ለኑሮ ተስማሚ የሆነ አካባቢን ለመፍጠር በተለይ ከተሞችን ከፕላስቲክ ቆሻሻ ነፃ ለማድረግ ባለስልጣኑ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል። የአካባቢ ብክለትን መከላከል ለአንድ ተቋም ብቻ የሚተው ባለመሆኑ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የእቅዳቸው አካል አድርገው ሊሰሩ እንደሚገባም ጠይቀዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የፌዴራል፣ የክልልና የዞን የሥራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳታፊ ሆነዋል።    
በሀረሪ ክልል በዘንድሮው አመት 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል
Apr 21, 2024 111
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 13/2016(ኢዜአ)፡- በሀረሪ ክልል በዘንድሮው አመት 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር እና የግብርና ልማት ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ሮዛ ኡመር ገለፁ፡፡ ወይዘሮ ሮዛ ኡመር የዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን አስመልክተው እንደገለፁት ከሚተከሉ ችግኞች መካከል ከ1 ነጥብ 7 ሚሊየን በላይ የተለያዩ አይነት ፍራፍሬዎች ናቸው፡፡ ይህም የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ አንፃር ጉልህ ፋይዳ እንዳለው ተናግረው በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረትና የአፈርና ውሃ ጥበቃን የሚያሻሽሉ ሌሎች የደን ዛፎች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። እንዲሁም በአሁኑ ወቅት በክልሉ እየተመናመኑ የሚገኙ የፍራፍሬ ዝርያዎች እንደሚገኙበትም ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅትም በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች የጎርፍ ተጋላጭነትን በሚቀንስና የችግኝ ፅድቀት መጠንን በሚያሳድግ መልኩ የተፋሰስ ልማት ስራ መሰራቱን ጠቅሰዋል። በክልሉ በሚገኙ የተለያዩ የችግኝ ጣቢያዎችም ለበርካታ ዜጎች የሥራ እድል መፍጠር መቻሉንም አንስተዋል። በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከሚተከሉ 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ችግኞች ውስጥ 70 በመቶው የጥምር ደን ሲሆን 30 በመቶው ደግሞ የደን ዛፍ መሆኑን ገልጸዋል። እየተደረጉ የሚገኙ ዝግጅቶችን በሚመለከት የችግኝ ጣቢያ ኃላፊዎችና ባለሙያዎችም ከወትሮው በተለየ መልኩ የተለያዩ ችግኞችን የማዳቀል ስራ እየተሰራ መሆኑን ገልፀው የተያዘው እቅድ እንዲሳካ በቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑን ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
በጋምቤላ ክልል የአካባቢ ብክለት በሰውና በተፈጥሮ ሃብቶች ላይ እያደረሰ ያለውን ጉዳት ለመቀነስ በጋራ መስራት ይገባል-- -ርዕሰ መስተዳድር ኡሞድ
Apr 20, 2024 144
ጋምቤላ ፤ ሚያዝያ 12/2016(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል የአካባቢ ብክለት በሰውና በተፈጥሮ ሃብቶች ላይ እያደረሰ ያለውን ጉዳት ለመከላከል የክልሉ ሕዝብ በትብብር ሊሰራ እንደሚገባ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኡሞድ ኡጁሉ ገለፁ። "ብክለት ይብቃ! ውበት ይንቃ!" በሚል መሪ ሀሳብ ለስድስት ወራት የሚተገበር የአካባቢ ብክለትን የመከላከል የንቅናቄ መርሃ ግብር በክልል ደረጃ ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት የአካባቢ ብክለት ችግሮችን ለመፍታት የደረቅና ፍሳሽ ቆሻሻ አወጋገድ ስርዓቶችን ማዘመን ያስፈልጋል። በክልሉ የአካባቢ ብክለት ችግሮች በሰው ጤና ላይ ከሚያደርሰው ጉዳት በተጨማሪ በተፈጥሮ ሃብቶች ላይ ከፍተኛ ውድመት እያደረሰ መሆኑን ገልጸዋል። የአካባቢ ብክለት በአየር፣ በውሃ፣ በአፈርና በሌሎችም የተፈጥሮ ሀብቶች ላይ እየደረሰ ያለውን ጉዳት ለመከላከል ኅብረተሰቡን በማሳተፍ እንዲሰራ ርዕሰ መስተዳድሩ አሳስበዋል። በተለይም የፕላስቲክ ብክለት የሚያስከትሉት ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ ምርቶቹን መልሶ ጥቅም ላይ በማዋል የጉዳት መጠኑን ለመቀነስ የተጀመረው ጥረት ተጠናክሮ እንዲቀጥል አስገንዝበዋል። ለንቅናቄው ውጤታማነት የክልሉ ህዝብ ተሳትፎ ሊጠናከር እንደሚገባ ያሳሰቡት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ የክልሉ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል እንደሚያደርግ ገልጸዋል። የፌዴራል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ተወካይ አቶ ሺፈራው ነጋሽ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት የፕላስቲክ ቆሻሻ በሰውና በእንስሳት ጤና ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ነው። በተጨማሪም የፕላሰቲክ ቆሻሻ በየብስና በውሃማ አካላት ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ በመጨመሩ ምክንያት ለአካባቢ ውበትና ለብዝሃ ህይውት መመናመን አሉታዊ ተጽዕኖ እያሳደረ መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የፕላስቲክ አጠቃቀምና አወጋገድ ስርዓቱን በማዘመን ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት በቅንጅት እንዲሰራ ጠይቀዋል። የክልሉ አካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ቢሮ ኃላፊ አቶ ሙሴ ጋጄት በዚሁ ጊዜ እንዳሉት በንቅናቄው የክልሉ ሕዝብ በአካባቢ ብክለት ዙሪያ በቂ ግንዛቤ በመያዝ ድርሻውን እንዲወጣ ለማድረግ ዝግጅት መደረጉን አስታውቀዋል። በአገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረው የአካባቢ ብክለት ንቅናቄ በሰዎችና በእንስሳት ላይ እየደረሰ ያለውን ጉዳት ለመቀነስና ለማስቀረት አቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል፡፡ በንቅናቄ ማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የክልሉ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች የዘርፉ ባለሙያዎችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል፡፡  
በምዕራብና ቄለም ወለጋ ዞኖች 747 ሚሊዮን የቡና ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል
Apr 20, 2024 127
ጊምቢ፤ሚያዚያ 12/2016 (ኢዜአ) በምዕራብና ቄለም ወለጋ ዞኖች ከ747 ሚሊዮን በላይ ምርታማና ፈጥነው ምርት የሚሰጡ የቡና ችግኞች ለመጪው ክረምት ተከላ መዘጋጀታቸውን የዞኖቹ ግብርና ጽህፈት ቤቶች አስታወቁ፡፡ የጽህፈት ቤቶቹ ሃላፊዎች ለኢዜአ እንዳስታወቁት ለተከላ እየተዘጋጁ ያሉት ችግኞች በምርምር ምርታማነታቸው የተረጋገጡና በአጭር ጊዜ ምርት ለመስጠት የሚችሉ ናቸው። ዘንድሮ የሚተከሉት ችግኞች አሁን በሄክታር ከአራት ኩንታል ያልበለጠ ምርት የሚሰጡትን የቡና ዝርያዎች ምርት ወደ ዘጠኝ ኩንታል እንደሚያሳድጉት አስረድተዋል።   በተጨማሪም ለአራት ዓመት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ምርት ስለሚሰጡ፣ይህም አሁን በአርሶ አደሩ እጅ ካሉት ዝርያዎች ምርት ለመስጠት የሚያስፈልገውን ጊዜ በሦስት ዓመታት ያሳጥሩታል ብለዋል። ችግኞቹ ከጅማ ቡና ምርምር ማዕክል የተገኙ ሲሆን፣ 'ጫላ' ፣'መና ሲቡ'፣'ሓሩ አንድ'ና 'ሲንዴ' ተብለው መሰየማቸውን ገልጸዋል፡፡ የዞኖቹ አርሶ አደሮች በግብርና ባለሙያዎች ምክርና ክትትል በመታገዝ የጉድጓድ ቁፋሮ፣ያረጁ የቡና የመንቀልና ሌሎች ለተከላ የሚያስፈልግ ዝግጅት እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የምዕራብ ወለጋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ቡናና ሻይ ልማትና ግብይት ቡድን መሪ አቶ ኤፍሬም መሥፍን እንደተናገሩት በዞኑ ከ401 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል። ዘንድሮ ለተከላ የተዘጋጁት የቡና ችግኞች በነባር የቡና መሬትና በ66ሺህ በላይ ሄክታር አዲስ መሬት ላይ እንደሚተከሉ ተናግረዋል፡፡ ይህም በዞኑ በቡና የተሸፈነው 550 ሺህ ሄክታር ወደ 615ሺህ ሔክታር እንደሚያሳድገው አስታውቀዋል፡፡ የቡና ችግኞቹ በ3ሺህ 352 የግልና በ74 የመንግሥት ችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች መዘጋጀታቸውን የቡድን መሪው ተናግረዋል፡፡ በተመሳሳይ በቄለም ወለጋ ዞን ከ346 ሚሊዮን በላይ የቡና ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ቡናና ሻይ ልማትና ግብይት ቡድን መሪ አቶ ታደሰ ጋሩማ አስታውቀዋል፡፡ ለተከላ እየተዘጋጁ ያሉት ችግኞች በ107 የመንግሥትና በ899 የግል ችግኝ ማፍያዎች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል፡፡ በዞኑ 467 ሺህ 301 ሄክታር መሬት በቡና ተክል መሸፈኑን አመልከተው፣ በየዓመቱም ወደ 1 ነጥብ 4 ሚሊየን ኩንታል የሚጠጋ ምርት እንደሚሰበሰብ አስታውቀዋል፡፡ የጊምቢ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ዱጉማ ያደሳ፣ በግማሽ ሔክታር መሬታቸው ላይ የቡና ችግኞች ለመትከል ዝግጅት ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡ ችግኞች ከመንግሥት ችግኝ ጣቢያ የወሰዷቸው ችግኞች በእጃቸው ካሉት የተሻለ ምርት እንደሚሰጡ ከግብርና ባለሙያዎች መረዳታቸውን ገልጸዋል፡፡ የላሎ አሳቢ ወረዳ አርሶ አደር አቶ ቡልቱማ ታምሩ፤ በግላቸው ከ3ሺህ በላይ የቡና ችግኞች በባለሙያ ምክር በመታገዝ እንዳዘጋጁ አመልክተዋል፡፡  
የፕላስቲክ ውጤቶች አጠቃቀምና አወጋገድን በማዘመን የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል ትኩረት ተሰጥቷል--ባለስልጣኑ
Apr 20, 2024 160
አርባ ምንጭ ፤ ሚያዝያ 12/2016 (ኢዜአ)፦ የፕላስቲክ ውጤቶች አጠቃቀምና አወጋገድ ስርአትን በማዘመን የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል ትኩረት መሰጠቱን የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። “ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ” በሚል መሪ ሃሳብ ክልል አቀፍ የብክለት መከላከል ንቅናቄ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል።   የባለስልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬነሽ መኩሪያ በተለይ ለኢዜአ እንደገለጹት የፕላስቲክ ውጤቶች አጠቃቀምና አወጋገድ ስርአትን በማዘመን ሀገርን ከአካባቢ ብክለት የጸዳች ለማድረግ በትኩረት ይሰራል። የፕላስቲክ ቆሻሻዎች በመሬት ውስጥ ለዘመናት ሳይበሰብሱ በመቆየት ስነ-ምህዳርን በማዛባት፣ ምርትና ምርታማነት በመቀነስ እንዲሁም የውሃ አካላትን በመበከል በሰውና በእንስሳት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እያስከተሉ ይገኛሉ ብለዋል። የፕላስቲክ ውጤቶች አካባቢን የመበከል፣ የማቆሸሽና መሠረተ ልማቶችን ከመጉዳት ባለፈ ለማህበረሰቡ የጤና ጠንቅ የሚሆኑበት ሁኔታ መኖሩንም ነው ያስረዱት። የፕላስቲክ ውጤቶች አጠቃቀምና አወጋገድ ሥርአት ላይ የባህሪ ለውጥ ባለመምጣቱ በሰው ልጆች ላይም ጉዳት እያደረሰ መሆኑንም ገልጸዋል። በመሆኑም የፕላስቲክ ውጤቶችን በአግባቡ የመጠቀምና የማስወገድ ሥራ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት እንደሚሰራ ወይዘሮ ፍሬነሽ ተናግረዋል። በአካባቢ ደህንነት መብት አዋጅ አንቀጽ 44 መሠረት ሁሉም ሰው ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ የመኖር መብት እንዳለው ጠቅሰው፣ የፕላስቲክ ውጤቶችን አወጋገድ በማዘመን የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል በቅንጅት ይሰራል ብለዋል። ዳይሬክተሯ እንዳሉት እንደ ሀገር የቆሻሻ አወጋገድ ስርአትን ለማዘመንና ቆሻሻን በመልሶ ዑደት ጥቅም ላይ ለማዋል በከተሞች የተጀመሩ ሥራዎችን ለማጠናከር ይሰራል። በእዚህ ረገድ የተጀመሩ ሥራዎችን በሁሉም የሀገሪቱ ከተሞች ለማስፋትና ለሥራ ዕድል መፍጠሪያነት ለማዋል ባለስልጣኑ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑንም አስረድተዋል። የፕላስቲክ ምርቶች ከሚሰጡት ጥቅም ይልቅ የሚያስከትሉት ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ ህብረተሰቡ በፕላስቲክ ምትክ ባህላዊ ቁሶችን መጠቀም እንዳለበት አስገንዝበዋል። እንደሀገር ቆሻሻ አወጋገድ ሥርአቱን ለማዘንም ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሰራም አስታውቀዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደን፣ አካባቢ ጥበቃና ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ግዛቴ ግጄ በበኩላቸው እንዳሉት የፕላስቲክ ቁሶች በሰው፣ በእንስሳትና በዕጽዋት ላይ ጉዳት እያስከተሉ ነው።   "የፕላስቲክ አጠቃቀማችን ኋላ ቀር በመሆኑ ፕላስቲኮችን በቸልተኝነት በየስፍራው እንጥላለን" ያሉት አቶ ግዛቴ፣ በዘፈቀደ የሚጣሉ ፕላስቲኮች በአካባቢ ስነ-ውበት ላይም አሉታዊ ጫና እየፈጠሩ ነው ብለዋል። የፕላስቲክ ውጤቶች አገልግሎት ከሰጡ በኋላ ለመልሶ ዑደት ካልዋሉ በነፋስና ጎርፍ ተወስደው ከተሞችን፣ የእርሻ ማሳዎችና የውሃ አካላትን ከመጉዳት ባለፈ የሰው ልጅ፣ የዱርና የቤት እንስሳትን የምግብ ሰንሰለት ያውካሉ ብለዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ የሚጣሉ የፕላስቲክ ቆሻሻዎች በጎርፍ ተወስደው በአባያና ጫሞ ሐይቆች መካከል ከ70 ሄክታር በላይ የደን ሀብትን ከጥቅም ውጭ ማድረጋቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል። እንደ ክልል ፕላስቲክ ቆሻሻን በመልሶ ዑደት ጥቅም ላይ ለማዋል፣ ፕላስቲኮችን መልሶ ለሌላ አገልግሎት ለመጠቀምና በምትኩ በቀላሉ ሊበሰብሱ የሚችሉ ምርቶችን ለመጠቀም ህዝባዊ ንቅናቄ መጀመሩንም ተናግረዋል። ህብረተሰቡ አካባቢውን ከብክለት በመጠበቅ የተጀመረው ንቅናቄ ከግብ እንዲደርስ ጠንካራ ተሳትፎ ሊያደርግ እንደሚገባም አቶ ግዛቴ አሳስበዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ “ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ” በሚል መሪ ቃል ሀገር አቀፍ የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄን ባለፈው መጋቢት ወር ማስጀመራቸው የሚታወስ ነው።      
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም