አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ የብዝኃ ሕይወት ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ እንዲውል ያስችላል
Mar 29, 2026 203
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 20/2018 (ኢዜአ)፡- የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ኢትዮጵያ ያላትን ዕምቅ የብዝኃ ሕይወት ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋል ገንቢ ሚና እንዳለው የዘርፉ ምሁራን ገለጹ፡፡ በአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የአካባቢ ሕጎችና ደረጃዎች ዴስክ ኃላፊ ወንደሰን ታደሰ፤ ኢትዮጵያ የውኃ፣ የደን፣ የዓየር ንብረት አገልግሎት፣ የቁጥጥርና ቱሪዝም ሥርዓተ-ምኅዳር ብትታደልም በሚገባት ልክ አልተጠቀመችም ብለዋል። የሥርዓተ-ምኅዳር ጉዳዮች በሰው ሠራሽና ተፈጥሯዊ ጉዳዮች በከፍተኛ ጫና ላይ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ በአገልግሎቱ አቅራቢዎችና ተጠቃሚዎች መካከል የጋራ መግባባትን በመፍጠር ዘላቂ የአካባቢ ጥበቃ ሥርዓትን ማጠናከር እንደሚያስችልም አስረድተዋል። የፋርም አፍሪካ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ሸዊት አማኑኤል በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያን የብዝኃ ሕይወት ሃብቶች ለሕብረተሰቡ ይበልጥ ጥቅም ላይ እንዲውሉ የሚያስችል ሥራ እያከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ የባሌ አካባቢ ማኅበረሰብ ተፈጥሮን በመንከባከብ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ተጠቃሚ መሆን መጀመሩን ገልጸው፤ ይህ በሁሉም አካባቢዎች መስፋት እንዳለበት አመላክተዋል። መንግሥት በአረንጓዴ ዐሻራና በአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራዎች ተጨባጭ ውጤቶች ማስመዝገቡን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ ያላትን የብዝኃ ሕይወት ሀብት ይበልጥ መለየትና ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ በመደ ወላቡ ዩኒቨርሲቲ የውኃ ሀብትና ሀይድሮሎጂ መምህር ዓለምአየሁ አባተ (ዶ/ር)፤ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ማኅበረሰቡ የሠራበትን እንዲያገኝ በማድረግ የተጠናከረ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ማከናወን ያስችላል ብለዋል፡፡ በባሌ ኢኮሎጂ በ20 ወረዳዎች በመሰማራት እየሠሩ መሆኑን የገለጹት የፋርም አፍሪካ ፕሮግራም ሥራ አስኪያጅ ፈይሳ አሰፋ፤ በኢትዮጵያ የካርበን ክፍያ መጀመሩ የሕብረተሰቡን የአካባቢ ጥበቃ ተነሳሽነት ያሳድጋል ብለዋል፡፡ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጁ ኢትዮጵያ ያላትን ሰፊ የብዝኃ ሕይወት ሀብት ጠብቃ እንድትቆይና ማኅበረሰቡ ተገቢውን ጥቅም እንዲያገኝ ያስችላል ሲሉም አስገንዝበዋል።
በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ ነው
Mar 28, 2026 110
አምቦ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በጽህፈት ቤት የደን ልማት ባለሙያ ጉደታ ጡሪ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ እየተዘጋጁ ከሚገኙ ችግኞች መካከል ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ዝርያዎች እንደሚገኙበት ተናግረዋል። በክረምቱ ወራት አጠቃላይ ከ94 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የችግኝ ተከላ እንደሚከናወን ገልጸው፤ የችግኝ ማፍላት ስራው በዞኑ በሚገኙ ሁሉም ወረዳዎች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ባሳተፈ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ዝግጅቱ የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንዲቻል ምርታማነታቸው ከፍተኛ በሆኑና በተሻሻሉ የችግኝ ዝርያዎች ላይ ትኩረት ማድረጉንም ጠቅሰዋል። ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሮች አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተው፤ ችግኞችን የመንከባከብና የመጠበቅ ስራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑንም አክለዋል። የተተከሉ ችግኞች የአካባቢ ስነ-ምህዳርን ከመቀየር አንጻር ከፍተኛ ሚና ከመጫወታቸው ባለፈ፣ ደርቀው የነበሩ ኩሬዎች ዳግም ውሃ እንዲይዙ በማድረግ ለአርሶ አደሩ ምቹ ሁኔታ ፈጥረዋል ነው ያሉት። ባለፉት ሰባት ዓመታት በድምሩ 616 ሺህ 613 ሄክታር መሬት ላይ ችግኞች መተከላቸውን አስታውሰው፤ የአካባቢው ማህበረሰብ ያለውን ደን የመጠበቅ ባህላዊ እሴት ለአረንጓዴ ልማት ስራው ስኬታማነት ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጉን ገልጸዋል።
ለቀጣዩ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ ነው
Mar 27, 2026 104
ሆሳዕና፤ መጋቢት 18/2018 (ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ ሻራ መርሐ-ግብር የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ደንና አካባቢ ጥበቃ ልማት ቢሮ አስታውቋል። የቢሮው ኃላፊ አብርሃም መጫ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ባለፉት 7 ዓመታት በክልሉ 450 ሺህ ሔክታር በአካባቢ ጥበቃና በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ማልማት ተችሏል። በዚህም የአፈር ለምነትን በማስጠበቅ፣ የግብርና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥን ጨምሮ በበርካታ ዘርፎች ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ መቻሉን አብራርተዋል። በዚህ ዓመትም 270 ሚሊየን የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸውን ችግኞች በመትከል 80 ሺህ ሔክታር መሬትን ለማልማት ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሠራን ነው ብለዋል። ሥነ-ምኅዳርን መሠረት ያደረጉ ለምግብነትና ለሌሎች ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የሚውሉ ችግኞችን የማፍላትና የማዘጋጀቱ ተግባር እየተከናወነ እንደሚገኝም ነው ያረጋገጡት።
የበልግ ዝናብ ስርጭት ለግብርና ምርታማነትና ለእንስሳት መኖ አቅርቦት ከፍተኛ ፋይዳ ያለው ነው-የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት
Mar 26, 2026 226
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2018(ኢዜአ)፦የዘንድሮው የበልግ ዝናብ ስርጭት በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ለሚከናወኑ የግብርና ስራዎች ስኬታማነትና ለእንስሳት መኖ አቅርቦት መሻሻል ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር የኢትዮጵያ ሚትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢንስቲትዩቱ የትንበያ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አሳምነው ተሾመ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ፤ ተቋሙ የአየር ጸባይ አዝማሚያዎችን፣አዎንታዊና አሉታዊ ተጽዕኖዎችን በወቅቱ ለማህበረሰቡና ለሚመለከታቸው ተቋማት የማድረስ ስራውን በልዩ ትኩረት እየከወነ ይገኛል። ከየካቲት እስከ ግንቦት ባለው የበልግ ወቅትም፣ በተለይም በሀገሪቱ ደቡባዊ አጋማሽ የዓመታዊ ዝናብ መጠኑ እስከ 55 በመቶ የሚሸፈንበት ዋነኛ ወቅት ነው ብለዋል። በ2018 ዓ.ም የበልግ ወቅት አብዛኞቹ የአገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ እንደሚያገኙ ተናግረዋል፡፡ እስካሁንም በ55 የሚደርሱ አካባቢዎች በ24 ሰዓት ውስጥ ከ35 እስከ 148 ሚሊ ሜትር የሚደርስ ከፍተኛ መጠን ያለው ዝናብ መመዝገቡን ገልጸዋል። ባለፉት ቀናት የታየው ተስፋ ሰጪ የዝናብ ስርጭት ለአርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች እንዳሉት ጠቅሰው፥ ለበልግ እርሻ ዝግጅትና ለዘር ስራ ምቹ ሁኔታን መፍጠሩንም ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም ለሰውና ለእንስሳት የመጠጥ ውሃ አቅርቦትን ማሻሻሉን እንዲሁም የእንስሳት መኖ ልማትን በማፋጠን ረገድ ከፍተኛ ድርሻ መኖሩ ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። በመጪዎቹ ሚያዝያና ግንቦት ወራትም በደቡብ፣ በደቡብ ምዕራብ፣ በመካከለኛውና በሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ ክፍሎች የበልግ ዝናብ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። በተለይም በደቡብና በደቡብ ምዕራብ አካባቢዎች ዝናቡ ዘግይቶ የሚወጣ በመሆኑ ለግብርናውና ለአካባቢ ጥበቃ ስራው ተጨማሪ ዕድል እንደሚፈጥር አስረድተዋል። ይሁን እንጂ፣ ከፍተኛ መጠን ያለው ዝናብ ወደ ጎርፍ አደጋ ሊቀየር ስለሚችል ማህበረሰቡና የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ቅድመ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል።
በጣና ሐይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም ለማጥፋት አዲስ የንቅናቄ ዘመቻ ተጀመረ
Mar 25, 2026 126
ባህር ዳር ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ በጣና ሐይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም ለማጥፋት አዲስ የንቅናቄ ዘመቻ ተጀመረ። የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በሐይቁ ህልውና ላይ አደጋ የደቀነውን የእምቦጭ አረም በተደመረ አቅም ለማስወገድ የትብብር ጥሪ አቅርቧል። ከጣና ሃይቅና አካባቢው የእምቦጭ አረምን ለማስወገድ የሚያስችል የንቅናቄ መርሃ ግብር በባህር ዳር ከተማ ሽንብጥ ቀበሌ የጣና ዳርቻ በዛሬው እለት በይፋ ተጀምሯል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ የተገኙት የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ሃላፊ አቶ ተስፋሁን አለምነህ፤ በጣና ሃይቅ ላይ እየተስፋፋ የመጣውን የእምቦጭ አረም በተባበረ ክንድ በማስወገድ የሃይቁን ህልውና መጠበቅ ይገባናል ብለዋል። አረሙን ለማጥፋት በሰው ኃይል እና በማሽን እንዲሁም አጠቃላይ የሕዝቡን ጠንካራ ተሳትፎ ማእከል ያደረገ ስራ የሚጠይቅ መሆኑን ገልጸዋል። የእምቦጭ አረም በቀላሉ የመስፋፋትና የማንሰራራት ባሕሪ ያለው በመሆኑ ቀጣይነት ያለው ዘመቻ እና የክትትል ስራ የሚያስፈልግ ስለመሆኑም አፅኖት ሰጥተዋል። በመሆኑም በሐይቁ ህልውና ላይ አደጋ የደቀነውን የእምቦጭ አረም በተደመረ አቅም ለማስወገድ እንዘጋጅ በማለት ኃላፊው ጥሪ አቅርበዋል። የመከላከል ሥራው በሰው ኃይልና በማሽነሪ በመታገዝ እንዲሁም ከባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር በባዮሎጂካል ዘዴ እየተከናወነ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።
ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ማሳካት በሚያስችል መልኩ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Mar 25, 2026 128
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2018(ኢዜአ)፦ በ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር የተያዘውን ሀገራዊ ግብ ማሳካት በሚያስችል መልኩ ውጤታማ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የአረንጓዴ አሻራ የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ(ዶ/ር) ገለጹ። አስተባባሪው ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ዘንድሮ የሚካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር፣ የመጀመርያው ምዕራፍ ማጠቃለያ ዓመት በመሆኑ ዝግጅቱ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡ በዚህም በዘንድሮው መርሃ-ግብር በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ7 ነጥብ 5 ቢሊየን ችግኝ በላይ ለመትከል እቅድ ተይዞ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት የተገኙ ተሞክሮዎችን በማስፋት የፍራፍሬ ችግኞችን የማስፋት፣ የሀገር በቀል ዝርያዎችን ቁጥር ከፍ የማድረግ ብሎም የእፅዋት አይነት ስብጥር በሰፊው እየተሰራበት መሆኑንም ገልፀዋል። በበጋው ወቅት የተከላ ቦታዎችን የመለየት፣ የተለዩ ቦታዎች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ የማከናወን፣ ከየአካባቢው አየር ንብረት ጋር የሚጣጣሙ ችግኞችን የማፍላትና የተለዩ ቦታዎች ላይ ካርታ የማዘጋጀት ስራ በስፋት መከናወኑን ነው ያስታወቁት። በዚህም በክልሎች እስካሁን 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ሄክታር መሬት ለችግኝ ተከላ የሚውሉ ቦታዎችን መለየታቸውን ጠቅሰው እስካሁን ከ110 ሺህ በላይ ችግኝ ጣቢያዎች ወደ ስራ ገብተው ችግኞች እያፈሉ ይገኛሉ ብለዋል። በዘንድሮው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ7 ነጥብ 5 ቢሊየን በላይ ችግኝ ለመትከል በእቅድ መያዙን ተናግረው እስካሁን 6 ነጥብ 1 ቢሊየን ችግኝ ዝግጁ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ በቀሪው ጊዜ የእንክብካቤ ተግባራት እንደሚከናወኑ ጠቅሰው ጉድጓድ የማዘጋጀት ስራዎችን ጨምሮ ሌሎችም እንደሚከናወኑ ገልጸዋል፡፡ ቀደም ሲል የነበረውን የክረምት ዝናብ ብቻ የመጠበቅ ልምድ መቀየሩን ጠቁመው ይህም ችግኞች ረጅም የዝናብ ወቅት እንዲያገኙ በማድረግ የፅድቀት መጠናቸውን በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚጨምረው አስረድተዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር አሁን ላይ የህዝቡ ባህል እየሆነ መምጣቱን ጠቅሰው በቀጣይም የዜጎችን የባለቤትነት ስሜት የማሳደግ እና የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
በክልሉ ከ458 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ተከናውኗል-ቢሮው
Mar 24, 2026 127
ባህርዳር ፤መጋቢት 15 /2018 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል በዘንድሮው የበጋ ወራት በአርሶ አደሩ ተሳትፎ በ458 ሺህ 794 ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ መከናወኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ ። የቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንደገለፁት በክልሉ በዘንድሮ የበጋ ወራት ከዘጠኝ ሺህ የሚበልጡ ተፋሰሶችን መሰረት ያደረገ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ ተካሂዷል። በዚህም ከ458 ሺህ 794 ሄክታር በላይ መሬት ላይ የማሳና የጋራ ላይ ዕርከን ስራዎችን መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። እንዲሁም ከ91 ሺህ ሄክታር በላይ የተራቆቱና የተጎዱ ተራራማ ቦታዎችን በመከለል ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተጠብቀው መልሰው እንዲያገግሙ መደረጉንም አመልክተዋል ። በተጨማሪም ከ7 ነጥብ 6 ሚሊዮን የሚበልጡ የተለያዩ የውሃ ማስረጊያ ስትራክቸሮች መከናወናቸውን ጠቁመው የውሃ ማፋሰሻና መቀልበሻ ቦዮች ግንባታ ስራዎችም መካሄዳቸውን ተናግረዋል ። አርሶ አደሩ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ የህልውና ጉዳይ መሆኑን በየጊዜው እየተረዳ በመምጣቱ ከዕቅድ በላይ ስራውን መፈፀም እንደተቻለም አስታውቀዋል። በመጭው የክረምት ወቅት በበጋ ወራት የተከናወነውን የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ በስነ-ህይወታዊ ዘዴ ለማጠናከር ከወዲሁ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አመላክተዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የሰከላ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ዓለሙ ይግዛው እንዳሉት የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ መስራት ከተጀመረ ወዲህ የተራቆቱ መሬቶች ደን መልበስ ጀምረዋል ። የእርሻ መሬቶችም የአፈር ለምነታቸው እንዲጨምርና የሰብል ምርታማነት እየተሻሻለ እንዲመጣ ማስቻሉንም ገልፀዋል። የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ የህልውና ጉዳይ በመሆኑ በየዓመቱ እየሰራን እንገኛለን ያሉት ደግሞ በአዊ ብሄረሰብ አስተዳደር ዞን የጓንጓ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር ሙሉነህ ይግዛው ናቸው። ባለፉት ዓመታት በሰራነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ ተፋሰሶች በማገገማቸው ለእንስሳት ዋነኛ የመኖ ምንጭ ሆነዋል ብለዋል።
የሚቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎትን በማዘመን የሚኖረውን ጠቀሜታ ለማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Mar 23, 2026 154
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦የሜቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎትን ዘመናዊና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለማድረግ የጀመራቸውን ስራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የተፈጥሮ ሃብት አገልግሎት አቅራቢዎች ለሥነ-ምኅዳር ደኅንነት በይበልጥ ሊተጉ ይገባል ኢንስቲትዩቱ ዓለም አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ ቀንን በኢትዮጵያ ለ45ኛ ጊዜ "ዛሬን መመልከት ፤ነገን ለመጠበቅ " በሚል መሪ ሀሳብ እያከበረ ይገኛል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተርና በዓለም አቀፉ የሚቲዎሮሎጂ ድርጅት የአፍሪካ አህጉር ፅህፈት ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ፈጠነ ተሾመ እንደገለጹት፤ የአየር ንብረት ለውጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት ላይ አሉታዊ ተፅእኖ እያሳደረ ያለ ጉዳይ ነው። በመሆኑም ተፅእኖውን መግታት የሚያስችል የሚቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎት አሰጣጥን ማጠናከር ዋነኛው ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ እያስመዘገበች ያለውን ፈጣን እድገት ለማስቀጠል የሚቲዎሮሎጂ መረጃ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ኢኒስቲትዩቱ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል አቅም መገንባት ላይ በትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በተለይም አጋር አካላትን ባሳተፈ መልኩ ተጨማሪ አቅም የሚፈጥሩ መሰረተ ልማቶችን ማስፋፋት፣ዘመኑን የዋጁ ቴክኖሎጂዎችን ጥቅም ላይ ማዋል እና የሰው ሀይል ልማት ዋና ዋናዎቹ ስለመሆናቸው አንስተዋል። በኢትዮጵያ ለ45ኛ ጊዜ የሚከበረው ዓለም አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ ቀን ስራዎችን ይበልጥ ለማጠናከርና ተደራሽነትን ለማስፋት አስቻይ ሁኔታ እንደሚፈጥር አክለዋል። በተጨማሪም ኢንስቲትዩቱ የሚሰጠውን አገልግሎት በዘመናዊ የሚቲዎሮሎጂ ሳይንስ ላይ በመመስረት ዛሬ የተሻለ መረጃ በመያዝ የተሻለ ነገን ለመገንባት የተለያዩ የጥናትና ምርምር ስራዎችን እየሰራ ስለመሆኑን ገልጸዋል።
የትራንስፖርት ዘርፉን ከአካባቢ ብክለት የጸዳ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል
Mar 23, 2026 142
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የትራንስፖርት ዘርፉን ከአካባቢ ብክለት የጸዳ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሐሰን ገለጹ፡፡ በባህር ዳር የአውሮፕላን ማረፊያ ማስፋፊያን ጨምሮ ግዙፍ መሠረተ ልማቶች ግንባታ እየተፋጠነ ነው ኢትዮጵያ በትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ መሰረተ ልማት፣በከተማ ትራንስፖርት እና አረንጓዴ ቴክኖሎጂዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ዘላቂ የትራንስፖርት ስርዓት ለመዘርጋት እየሰራች ትገኛለች። ይህንን ለመደገፍ ታዳሽ የኃይል ምንጭ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችን ማስፋፋትና ዘርፉን ማበረታታት ከተሽከርካሪ የሚለቀቀውን በካይ ጋዝ ለመቀነስ ያስችላል። የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሐሰን ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ዘርፉ አካባቢን እንዳይበክል ከማድረግ አኳያ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል፡፡ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለሚያስመጡና ለሚገጣጥሙ አካላት አተገባበርን በተመለከተ ፖሊሲ ተዘጋጅቶ ተግባራዊ እየተደረገ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ በዚህ ከቀረጥ ነጻን ጨምሮ ልዩ ልዩ ማበረታቻዎች እየተደረገላቸው መሆኑን አንስተዋል፡፡ በነዳጅ የሚሰሩ ከሁለት እግር እስከ የከተማ ባስ እና የጭነት ተሽከርካሪዎች ድረስ ወደ ሀገር እንዳይገቡ ክልከላ መደረጉንም ተናግረዋል፡፡ ይህ እርምጃ ኢትዮጵያ ለዓለም የአየር ንብረት መጠበቅ ያላትን ቁርጠኝነት ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡ በአስር ዓመቱ ስትራቴጂ የልማት እቅድ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ500 ሺህ በላይ ተሽካርካሪዎች የታዳሽ ኃይል አማራጭን እንዲጠቀሙ ለማድረግ ታስቦ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ታዳሽ የኃይል አማራጭን የሚጠቀሙ የተሽከርካሪዎች ቁጥር 115 ሺህ መድረሱን ተናግረዋል፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የትራንስፖርት ዘርፉን ከአካባቢ ብክለት የጸዳ ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን አመላክተዋል፡፡ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ፖሊሲ የትራንስፖርት ዘርፉ አካባቢን እንዳይበክል ከማድረግ ባሻገር ታዳሽ የኃይል አማራጭ ላይ ትኩረት እንዲደረግ እና የነዳጅ ጥገኝነትን ለመቀነስ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ እንደ የነፋስ ኃይል፣ የኃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ የተፈጥሮ ጋዝ እና ሌሎች የታዳሽ ኃይል አማራጮች በስፋት መገኘት ከነዳጅ ተሽከርካሪዎች ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚደረገውን ሽግግር አስተማማኝ እንዳደረገው ጠቁመዋል፡፡
የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው - አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ
Mar 21, 2026 140
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሌሎች ሀገራት ትልቅ መነሳሳትን የሚፈጥርና ምሳሌ የሚሆን ፕሮጀክት ነው ሲሉ በኢትዮጵያ የኮሎምቢያ አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተጀመረው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እስካሁን ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ተተክለዋል። ይህም የአካባቢ ጥበቃን ከማጠናከር ባለፈ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ብዝሃ ህይወትን ለመጠበቅ ትልቅ ሚና እየተጫወተ ነው። ይህ መርሃ ግብር በአፍሪካ ቀዳሚ የሆነ ግዙፍ የደን ልማትና የተፈጥሮ ጥበቃ ዘመቻ ሲሆን የካርቦን ልቀትን በመቀነስ ረገድም በምሳሌነት ተጠቃሽ ነው። ሀገሪቱ የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም የተፈጥሮ ሥርዓት እንድትገነባ እያገዘም ይገኛል። በኢትዮጵያ የኮሎምቢያ አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ ለኢዜአ በሰጡት ቃለ ምልልስ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሚመራው የአረንጓዴ አሻራ ፖሊሲ እጅግ የሚደነቅ ጥረት ነው ብለዋል። አረንጓዴ አሻራ ለሌሎች ሀገራትና መሪዎች አርአያ የሚሆን ተሞክሮ እንደሚሆን ጠቁመው ይህ ተግባር ሁላችንም በጋራ እንድንሰራ ያበረታታናል ነው ያሉት። የሀገራት መሪዎች በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት እየመጡ ያሉ ተግዳሮቶችን ለዜጎች በግልጽ ማሳወቅ እንዳለባቸውና ይህም ዜጎች ለመፍትሄው እንዲሰሩ ያደርጋል ሲሉ ገልጸዋል። በተጨማሪም ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2027 የሚካሄደውን 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 32) እንድታስተናግድ መመረጧን አምባሳደሩ አድንቀዋል። ኮሎምቢያ እ.ኤ.አ. በ2024 የኮፕ 16 ጉባኤን ማስተናገዷን አውስተው ኢትዮጵያ ኮፕ 32ን በምታዘጋጅበት ወቅት ሀገራቸው ያካበተችውን ልምድ ለማካፈል ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል። አምባሳደሩ አክለውም የኮሎምቢያን ተሞክሮና የኢትዮጵያን የወደፊት ራዕይ በማጣመር፣ ተግዳሮቶችን በጋራ ለመፍታት ይሰራሉ ብለዋል።
የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ለሚያሻሽሉ መመሪያዎች ተፈፃሚነት ጥብቅ ቁጥጥር ይደረጋል
Mar 21, 2026 147
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ የሚያሻሽሉ መመሪያዎችን በማውጣት ለተግባራዊነታቸው ጥብቅ ቁጥጥር እንደሚደረግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢዎችና የአካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ከፋርም አፍሪካና ኤስ.ኦ.ኤስ ሳህል ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በሥርዓተ ምህዳር አገልግሎት ክፍያ ትግበራ ላይ ትኩረት ያደረገ የውይይት መድረክ አካሂዷል፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የባለድርሻ ተቋማትን ትብብር በማጠናከር በደንብ ቁጥር 545/2016 በተሰጠው ኃላፊነት መሰረት የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ሥርዓትን ይከታተላል፤ ይቆጣጠራል፡፡ የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ተፈጥሮ የቸራትን ዕምቅ የብዝኅ ህይወት ሃብት በሚገባት ልክ ጥቅም ላይ እያዋለች እንዳልሆነ ገልጸዋል። ለዚህም የውሃና የየብስ የሥነ-ምኅዳር ጸጋዎች ለሀገር የኢኮኖሚ ጥቅም ለማዋል የሚስችል "የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ቁጥር 140/2018" ተግባራዊ መደረጉን አስታውቀዋል። ምክር ቤቱም ከመንግስተና የዘርፉ ተዋናዮች ጋር የግብዓት ማሰባሰቢያ መድረኮችን በማዘጋጀት ግብዓት ታክሎበት አዋጁን በማፅደቅ ሥራ ላይ እንዲውል መደረጉን ተናግረዋል። በዚህም የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ለማሻሻል የሚረዱ የማስፈጸሚያ ደንቦችና መመሪያዎች መውጣታቸውንና ተፈፃሚነ መሆናቸውን ጥብቅ ክትትል እንደሚደረግ አንስተዋል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ንጉሱ ለማ፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተቀናጀ የሥነ-ምህዳር አገልግሎት የክፍያና የሕግ ማዕቀፍ እንዳለነበረ ገልጸዋል፡፡ በዚህም የኢትዮጵያ ሥርዓተ ምኅዳር ዘላቂነት ለማስጠበቅ የመንግስትና የባለድርሻ ተቋማትን ፍላጎት ታሳቢ ያደረገ የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ቁጥር 140/2018 መፅደቁን ተናግረዋል። የአገልግሎት ክፍያ የአሰራር ሥርዓቱም የኢኮኖሚ ዕድልን በመፍጠርና ለአገልግሎቱ አቅራቢዎች ዘላቂ ዋስትናን ይፈጥራል ብለዋል፡፡ አዋጁን መነሻ በማድረግ የዘርፉን ተዋናዮች ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል የማስተግበሪያ መመሪያ መዘጋጀቱን አስረድተዋል። የፋርም አፍሪካ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ሸዊት አማኑኤል፤ ኢትዮጵያ ደኖችን በመንከባከብ የበካይ ጋዝ ልቀትን በመቀነስ ለዓለም የከባቢ አየር ሥነ ምህዳር ገንቢ ሚና እየተወጣች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያዊያን ደንን በመንከባከብ በአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ በሚበረክቱት አስተዋፅኦ ልክ ሳይንሳዊ ጥናትና ኦዲት ተካሂዶ ገቢ ማመንጨት መጀመሩን አንስተዋል። የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ በባሌ አካባቢ የተጀመረውን በሌሎች አካባቢዎች ለማስፋት በር የሚከፍት መልካመ ዕድል መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የደን ሽፋንን በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ ይገኛል
Mar 21, 2026 110
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን የደን ሽፋን በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ እንደሚገኝ የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ። የፌዴራልና የክልል መንግስታት የግብርና ዘርፍ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ''የመደመር መንግሥት የተፈጥሮ ሃብት ዕይታ'' በሚል መሪ ሃሳብ የዓለም አቀፍ የደን ቀን የምክክር መድረክ ተካሂዷል፡፡ በመድረኩ የግብርና ሚኒስትር አቶ አዲስ አረጋ፤ የመደመር መንግሥት ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሰጠው ትኩረት የተፈጥሮ ሃብቶችን በማስጠበቅ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማበርከት ያስቻለ ውጤት መገኘቱን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል የኢትዮጵያን የደን ሽፋን ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ማሳደግ እንደተቻለ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የተራቆተ የመሬት ገፅታ በደን በመሸፈን የአፈር መሸርሸርና የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን መጠበቅ ያስቻለ ውጤት እየተገኘ መሆኑንም አንስተዋል። ቡናን ጨምሮ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞች የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከቱ እንደሚገኝ አብራርተዋል። በቀጣይም የማህበረሰቡን የደን ጥበቃ ግንዛቤ በማሳደግና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በማስቀጠል በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርና የደን ልማት ስኬትም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቀነስ የግብርና ምርታማነትን እያሳደገ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ለአብነትም ከሰባት ዓመታት በፊት ወደ ውጭ ይላክ የነበረን 230 ሺህ ቶን የቡና ምርት አሁን ላይ ወደ 475 ሺህ ቶን በማሳደግ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ማግኘት እንደተቻለ አንስተዋል። የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር ከበደ ይማም በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ የደን ሃብት ልማት መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያስገኘ ነው ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬታማነትም ከክልልና ባለድርሻ ተቋማት ጋር በቅንጅት መሰራቱን አንስተዋል። የአረጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር)፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያስገኘውን ስኬትና ቀጣይ ሥራ የሚዳስስ የመነሻ ጽሁፍ አቅርበዋል። ይህም የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የዓባይ ተፋሰስ ወረዳዎችን የተራቆተ የመሬት ገፅታ በደን በመሸፈን የከርሰና የገፀ ምድር ሃብቶች ላይ ዘርፍ ብዙ ጠቀሜታ እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል።
የተፈጥሮ ሃብት አገልግሎት አቅራቢዎች ለሥነ-ምኅዳር ደኅንነት በይበልጥ ሊተጉ ይገባል
Mar 21, 2026 121
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፡- የተፈጥሮ ሃብት አገልግሎት አቅራቢዎች የአካባቢ ጥበቃ ባህልን በማሳደግ ለሥነ-ምኅዳር ደኅንነት ይበልጥ ሊሠሩ እንደሚገባ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን አሳሰበ። ባለሥልጣኑ ከፋርም አፍሪካ እና ኤስ.ኦ.ኤስ ሳህል ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ትግበራ ላይ ትኩረት ያደረገ የውይይት መድረክ እያካሄደ ነው። በዚሁ ወቅትም የባለሥልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ንጉሡ ለማ፤ ተቋማቸው የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ሥርዓትን የመከታተልና የመቆጣጠር ኃላፊነት እንዳለበት ገልጸዋል። በዚህም የኢትዮጵያን ሥርዓተ-ምኅዳር ዘላቂነት ለማስጠበቅ የመንግሥትና የባለድርሻ ተቋማትን ፍላጎት ታሳቢ ያደረገ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ቁጥር 140/2018 መጽደቁን አስረድተዋል። የሥርዓተ-ምኅዳር የአገልግሎት ክፍያ የአሠራር ሥርዓቱም ለተጠቃሚዎችና አገልግሎት አቅራቢዎች ምቹ የክፍያ መፈጸሚያ ሁኔታ እንደፈጠረ አረጋግጠዋል። ይህም የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት አቅርቦትን በማሻሻልና ዘላቂነት እንዲኖረው ከፍተኛ እገዛ ያደርጋል ብለዋል። አዋጁም ከዚህ በፊት ክፍያ ያልተተመነላቸው የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎቶች ላይ የዋጋ ተመን በማስቀመጥ የኢኮኖሚ ዕድልን እንደሚፈጥር አስረድተዋል። ለአዋጁ ገቢራዊነት የዘርፉ ተዋንያን ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ባለሥልጣኑ ለአዋጁ ማስፈጸሚያነት የሚየገለግሉ መመሪያዎች ማዘጋጀቱን አስታውቀዋል።
ለነዋሪዎቿ ምቾትን የፈጠረው የአዲስ አበባ አዲሱ ገጽታ
Mar 19, 2026 153
አዲስ አበባ እየተዋበች፤ እየደመቀች ነው። ለተሽከርካሪዎች ብቻ ሳይሆን ለእግረኞችም ምቹና ሰፋፊ ጎዳና ገንብታለች። ይህን የስልጡንነት አክሊል የተቀዳጀችው ይህች መዲና ልክ እንደ ስሟ መልክና ግብሯ አጊጧል። ዛሬ ላይ የመዲናዋ አውራ ጎዳናዎች በግራና በቀኝ በእግረኛ መንገዶች የታጀቡ ናቸው። በእግሩ የሚጓዝ ነዋሪም ይሆን ጎብኚ በመዲናዋ ዞር ዞር ቢል የከተማነትን ክብርና የሰው ልጅን ነጻነት የሚያውጅ አዲስ የከተማ ልማትን በተግባር ይመለከታል። ለወትሮው በጠባብ የእግረኛ መንገዶች፣ ለትራፊክ በማይመቹ አውራ ጎዳናዎች ትታወቅ የነበረችው መዲና፣ ዛሬ በኮሪደር ልማት አማካኝነት መልኳን እየቀየረች ትገኛለች። ይህ ልማት የከተማዋን ውበት ከማድመቅ ባለፈ፣ የነዋሪዎቿን የዕለት ተዕለት ሕይወት ምቹ፣ ቀላልና ስሉጥ አድርጎታል። በመዲናዋ የከተማ አኗኗርና የመንገድ አጠቃቀም ባህልም እየተቀየረ መሆኑን ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች ይገልጻሉ። በመዲናዋ ቀደም ባሉት ጊዜያት በእግር ለመጓዝ ምቹ መንገድ ባለመኖሩ ጉዞው አድካሚና አሰልቺ ነበር። ዛሬ ግን ሁኔታዎች ተቀይረዋልም ነው ያሉት። ይህም የእግር ጉዞን ማድረግ ያለውን የጤና ገፀበረከት እንድንቋደስ እያደረገን ነው ብለዋል በእግራቸው ሲጓዙ ያገኘናቸው ነዋሪዎች። የከተማዋ ነዋሪ የሆኑት ነጋ ፍቅሬ እንደሚሉት፣ የኮሪደር ልማቱ አዲስ አበባን ለእግረኞችና ብስክሌት ለሚጠቀሙ ተጓዦች ምቹ አድርጓታል። መንገዶቹ ለእግር ጉዞ እጅግ ምቹ ናቸው፤ በቀላሉ ለመንቀሳቀስና ለመዝናናትም አማራጭ ሆነዋል፤ ያሉት አቶ ነጋ ከቦታ ቦታ መንቀሳቀሻነት ባለፈ በየዳርቻቸው ለዓይን የሚማርኩ ሥፍራዎችን ያካተቱ መሆናቸውን አንስተዋል። የአዲስ አበባ ልማት ስኬት ግን ከዚህም በላይ ነው፤ በአካታችነቱ የሚወደሥ ተጨባጭ ለውጥ በመዲናዋ ጎላ ብሎ ይታያል። መምህር ጌታ ጫኔ ማየት የተሳናቸው ናቸው። ለእርሳቸው በመዲናዋ በእግር ከቦታ ቦታ መጓዝ ቀደም ሲል ትልቅ ፈተናና ስጋት ነበር። የኮሪደር ልማት ግን የእርሳቸውንና መሰል አካል ጉዳተኛ ዜጎችን ፍላጎት ታሳቢ ያደረጉ መንገዶችን እውን አድርጓል። ይህም በተለይ ለዓይነ ሥውራን የህብረተሰብ ክፍሎች ትልቅ እፎይታን የፈጠረ ነው። መምህር ጌታም ይህንኑ በማጠናከር ይህ ልማት ለእኛ ትልቅ ትርጉም አለው። የአካል ጉዳተኞችን ተጠቃሚነት ያረጋገጠ፣ በምቾት ሳንሳቀቅ እንድንቀሳቀስ ያስቻለንና ትልቅ የመንገድ ደህንነት ስጋታችንን የቀረፈ ስራ ነው ብለዋል። በሌላ በኩል የኮሪደር ልማቱ መዲናዋን ወደ ተሻለ የዕድገት ምዕራፍ እንዳሸጋገራት የሚናገሩት ወይዘሮ መንበረ አግዘው ናቸው። አዲስ አበባ አሁን ለመኖርም ሆነ ለመዝናናት ተመራጭ መዲና ሆናለች ይላሉ። አቶ ዘሩ ተገኝ በበኩላቸው የተዘረጋው መሠረተ ልማት ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል ታሳቢ ያደረገ መሆኑ አዲስ አበባ ለነዋሪዎቿ ምቹና ሰው ተኮር ልማቶች የሚከናወኑባት ከተማ እንድትሆን አድርጓታል ይላሉ። የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት የአፍሪካ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን በሚመጥን መልኩ ገፅታዋን ከመቀየር ባለፈ፣ ለአካል ጉዳተኞች ደህንነቱ የተጠበቀ መንገድ፣ የእግር ጉዞ ለሚያዘወትሩ ደግሞ ሰፊና ማራኪ ጎዳናን ፈጥሯል።
የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በዜጎች አኗኗር እና ጤና ላይ መሰረታዊ ለውጥ እያመጣ ነው
Mar 19, 2026 236
ወልቂጤ፤መጋቢት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በዜጎች አኗኗር እና ጤና ላይ መሰረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑን የጤና ዘርፍ የስራ ሃላፊዎች ገለጹ። አዋጁ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግብ ለማድረስ ያግዛል የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ በሀገሪቱ የቆሻሻ አወጋገድ ስርዓትን ለማሻሻል፣ የከተሞችን ውበት ለመጠበቅ እና ለዜጎች ምቹ የመኖሪያ አካባቢን ለመፍጠር ያለመ ሀገራዊ ዘመቻ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነት የተጀመረው ኢንሼቲቭ በሁሉም የሀገሪቷ አካባቢዎች ተግባራዊ እየተየደረገ ያለ መሆኑ ይታወቃል። የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ዋነኛ ዓላማም በተለይም በከተሞች የሚታየውን የንፅህና ጉድለት በማስተካከል ለነዋሪዎችና ለጎብኝዎች ዘመናዊና ምቹ ከተሞችን የመፍጠር ነው። በዚህም መሰረት የተገነቡ መሠረተ ልማቶችን በአግባቡ መጠገንና መጠበቅ፣ የቆሻሻ አወጋገድን የማዘመን፤ የመፀዳጃ ቤቶችን የማስፋትና የማዘመን ስራ በስፋትና በጥራት ማከናወን ተችሏል። ከዚህ አንፃር በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በፅዱ ኢትዮጵያ ኢንሼቲቭ የተገኘውን ውጤት በተመለከተ የኢዜአ ሪፖርተር የጤና ዘርፍ ሃላፊዎችንና ነዋሪዎችን አነጋግሯል። የጉራጌ ዞን ጤና መምሪያ ሃላፊ አየለ ፈቀደ፤ በኢንሼቲቩ በገጠርም ይሁን በከተሞች ሰፊ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸው ለስኬቱ በየደረጃው ያሉ የስራ ሃላፊዎችና አጠቃላይ የማህበረሰቡ ተሳትፎ የላቀ መሆኑን ገልጸዋል። ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ብዙ ተያያዥ የሆኑ ማህበራዊና የምጣኔ ሃብት ጥቅሞች እያስገኘ መሆኑን የገለጹት ሃላፊው በቀጣይም በተጠናከረ መልኩ ይቀጥላል ብለዋል። የአካባቢ ጽዳትና ውበትን በጋራ በመጠበቅና በመንከባከብ ምቹና ተመራጭ አካባቢ ለመፍጠር ዜጎችን በማሳተፍ ስኬት እየተመዘገበ ነው ብለዋል። በሁሉም የዞኑ አካባቢዎች ፅዱ እና ለመኖርያነት ምቹ የሆኑ መንደሮች እንዲሁም ሜዳ ላይ ከመፀዳዳት ነፃ የሆነ አካባቢ ለመፍጠር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። እስካሁን በዞኑ ከሚገኙ 315 ቀበሌዎች መካከል 70 በመቶ ያህሉ የዚህ ኢንሼቲቭ ትግበራ ተጠቃሚዎች መሆን መቻላቸውንም ለአብነት አንስተዋል። የሃድያ ዞን ጤና መምሪያ ሃላፊ ዶ/ር ደሳለኝ ሽጉጤ፤ የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በየአካባቢው ካለው ማህበረሰብ ባለፈ ከጤና፣ ከትምህርት እና ከሃይማኖት ተቋማት ጋር በቅንጅት መሰራቱ ውጤት አምጥቷል ብለዋል። የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በዞኑ ህዝብ ጤና እና አኗኗር ላይ ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ በመሆኑ ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ተናግረዋል። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ጤና መምሪያ ሃላፊ ሰለሞን ጉግሳ፤ የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በዞኑ በርካታ ቀበሌዎች እና ወረዳዎችን ጽዱ አካባቢ ማድረግ አስችሏል ብለዋል። የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ሃላፊ ሳሙኤል ዳርጌ፤ የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በክልሉ መሰረታዊ የሚባል ውጤት የመጣበት ስኬታማ ትግበራ መሆኑን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩ የተሻሻሉ መፀዳጃ ቤት በመገንባት የሰውና እንስሳ መኖርያ በመለየት ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር እያስቻለ ነው ብለዋል። በመሆኑም የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በክልሉ ዜጎች አኗኗር እና ጤና ላይ መሰረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑን አንስተው ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል። በጉራጌ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች ነዋሪዎችም የፅዱ አካባቢ ልማት በቆሻሻ አወጋገድና አጠቃቀም ላይ መሰረታዊ ለውጥ ማምጣቱን ተናግረዋል።
ለሀገራዊ የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ ትግበራ የባለድርሻ አካላት ቅንጅት መጠናከር አለበት
Mar 18, 2026 176
አዲስ አበባ፤መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ ስኬታማ ለማድረግ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎና ቅንጅት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ገለጹ። ባለስልጣኑ የፍኖተ ካርታውን ትግበራ ውጤታማ ለማድረግ ከተለያዩ የፌዴራል ተቋማት ጋር በጋራ መስራት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ(ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ባለስልጣኑ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል፡፡ በዚህም ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ለውጥ የሚያመጡ የህግና አሰራር ስርዓት ወደ ተግባር በማስገባት ለሌሎች ሀገሮች ምሳሌ የሚሆኑ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ገልፀዋል። የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ልማት ግቦችን ለማሳካትና ወደ ሰርኩላር ኢኮኖሚ የሚደረገውን ሽግግር ማፋጠን የሚያስችለው ሀገራዊ ፍኖተ ካርታ በ2017 ዓ.ም ተዘጋጅቶ ወደ ትግበራ መገባቱን አስታውሰዋል። ፍኖተ ካርታው ፅዱ ኢትዮጵያን በመፍጠር ሂደት ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ የማዋል(Recycling) ባህልን የሚያበረታታ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን በማጎልበት፣ ለተሻለ ኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታን በመፍጠርና አዳዲስ የስራ እድሎችን በመክፈት የሀገርን ኢኮኖሚ ለማሳደግ ጉልህ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የአካባቢ ጥበቃ ስራ በአንድ ተቋም ብቻ ውጤታማ ማድረግ ስለማይቻል የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት እንደሚጠይቅ ጠቅሰዋል። በዚህም ወደ ሰርኩላር ኢኮኖሚ የሚደረገው ሽግግር እንዲፋጠን ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቁርጠኝነትና በተጠናከረ ተሳትፎ የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። ከተቋማቱ ጋር የተደረገው ስምምነት በአካባቢ ጥበቃ ስራዎች ላይ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ተግባራትን ማከናወን፣ የህግና አሰራር ማሻሻያዎች፣ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ስርዓትን በቴክኖሎጂና በዕውቀት መደገፍ እንዲሁም የጋራ የድጋፍና ክትትል ስራዎችን በቅንጅት መስራት ከሚከናወኑ ሥራዎች መካከል ናቸው ብለዋል፡፡ ስምምነቱን ከተፈራረሙ ተቋማት መካከል የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን እንደገለጹት በባለስልጣኑ የተዘጋጀው ፍኖተ ካርታ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ ትልቅ ፋይዳ አለው፡፡ በሀገሪቱ የሚከናወኑ ግንባታዎች በመልሶ መጠቀም የተዘጋጁ የሀገር ውስጥ ግብዓቶችን እንዲጠቀሙ በትኩረት እንደሚሰራ ተናግረዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሃሰን መሃመድ በበኩላቸው የተዘጋጀው ፍኖተ ካርታ ከኢንዱስትሪ ዘርፉ ፖሊሲ ጋር የሚቀናጅ በመሆኑ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል። የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አለበል ደሴ በበኩላቸው ኢንስቲትዩቱ የፖሊሲ ፋይዳ ያላቸው ሀገራዊ ጥናቶችን በመለየት ፖሊሲ አውጪውን የማማከር ስራ የሚሰራ ተቋም እንደመሆኑ ለፍኖተ ካርታው ትግበራ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት የዋና ዳይሬክተር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሳባ ዘሪሁን በበኩላቸው በዚህ ስራ ባለድርሻ እንደመሆናችን የበኩላችንን አስተዋጽኦ ለማበርከት ዝግጁ ነን ብለዋል።
የአዲስ አበባ ኮሪደርና የአረንጓዴ ልማት ስኬቶች ለአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ዕድገት ትምህርት የሚሰጥ ነው
Mar 18, 2026 157
አዲስ አበባ፤መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ኮሪደርና የአረንጓዴ ልማት ስኬቶች ለአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ዕድገት ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን የዛምቢያና ኢስዋቲኒ የአካባቢ ጥበቃ ሙያተኞች ገለጹ። በአዲስ አበባ የተገነቡ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራ መዲናዋን ውብ ገፅታ በማላበስ ለነዋሪዎችና ጎብኝዎች ምቹ የእንቅስቃሴ ምኅደር ፈጥረዋል። በመዲናዋ በአጭር ጊዜ የተመዘገቡ የልማት ውጤቶችም አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅናን በማስገኘት ልምድና ተሞክሮ እየተቀሰመባቸው ይገኛል። በአዲስ አበባ የተጀመረው የኮሪደር ልማትም ከተማዋን ውብ ገፅታ በማላበስ ነዋሪዎችን ምቹና የአረንጓዴ ከባቢ በማጎናጸፍ በ75 የኢትዮጵያ ከተሞች እየተተገበረ ይገኛል። የዛምቢያና የኢስዋቲኒ የአካባቢ ጥበቃ ሙያተኞች ለኢዜአ እንዳሉት፤ አዲስ አበባ ከተማ የአፍሪካዊያን ማዕከልነቷን በተግባር ያረጋገጡ የልማት ውጤቶች ተገኝተዋል። በመዲናዋ በአጭር ጊዜ የተገነቡ አስደናቂ የልማት ውጤቶችም ከተማዋን ውብ ገፅታ በማላበስ ምቹ የከተሜነት ምኅዳር እንዲፈጠር ማድረጉን ገልጸዋል። በዛምቢያ የአካባቢና የገጠር ልማት ሚኒስቴር የደረቅ ቆሻሻ አስተዳደር ባለሙያ ብሬን ሲያካበያ፤ አዲስ አበባ ከጥቂት ዓመታት በፊት የተጎሳቆለና እርጅና የተጫጫነው ገፅታ እንደነበራት አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት በአጭር ጊዜ ውስጥ በአዲስ አበባ የተገነባው የኮሪደር ልማት ነዋሪዎች ምቹና ፅዱ የአረንጓዴ ከባቢን ያጎናጸፈ አስደናቂ ለውጥ መምጣቱን ገልጸዋል። የመዲናዋ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችና ሰማይ ጠቀስ ህንፃዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውም ውብ የከተሜነት ገፅታን በመፍጠር ልዩ ድምቀት እንደፈጠሩ ተናግረዋል። በህዝብና በአመራር ቁርጠኝነት ተገንብተው የተጠናቀቁት የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶችም ሀገራቸውን ጨምሮ ለአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ዕድገት ትልቅ ትምህርት መሆኑን አንስተዋል። የኢስዋቲኒ የአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ የኢኮኖሚ ባለሙያ መሎሰም ቡሊ በበኩላቸው፣ ከተሜነት የአንድ ሀገር የዕድገትና ስልጣኔ መገለጫ ነው ብለዋል። በአዲስ አበባ በአጭር ጊዜ የተገኙ ተምሳሌታዊ የኮሪደርና የአረንጓዴ ልማት ስኬቶች ዜጎች ዘመናዊ የከተሜነት አኗኗር ሥርዓት እንዲጎናጸፉ ያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። የመዲናዋ አስደናቂ የከተማ ውበት፣የአረንጓዴና ቆሻሻ አያያዝ የልማት ስኬቶች የአፍሪካን የአየር ንብረት ለውጥና የአካባቢ መራቆት የመቀነስ ግብ ያገናዘቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ልማትም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቀነስ አህጉራዊ አጀንዳዎችን የሚያሳካና ትምህርት የሚቀሰምበት መሆኑን አንስተዋል።
በአሪ ዞን ማኅበረሰቡን ያሳተፈ የጎርፍ እና የናዳ ቅድመ መከላከል ሥራ እየተከናወነ ነው
Mar 18, 2026 215
ጂንካ፤ መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አሪ ዞን ለጎርፍ እና ለናዳ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ማኅበረሰቡን በማሳተፍ አደጋን ቅድመ የመከላከል ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ አደጋ ሥጋትና ሥራ አመራር ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ አደጋ ሥጋትና ሥራ አመራር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አስራት አበበ እንደገለጹት፤ በአሪ ዞን የሚገኙ አራት ወረዳዎች በመልክዓ ምድራዊ አቀማመጣቸው ተራራማና ተዳፋት በመሆናቸው በተደጋጋሚ ለናዳ አደጋ ተጋላጭ ናቸው። በተመሳሳይ በዞኑ የሚገኙ ሦስት ከተሞች ደግሞ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ባለፈው ዓመት ወቅት በዎባ አሪ ወረዳ በተከሰተ የአፈር መንሸራተት በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን ያስታወሱት ኃላፊው፤ በዘንድሮው ዓመትም በደቡብ አሪ ወረዳ ወሰት ቀበሌ መሰል አደጋ መከሰቱን ተናግረዋል። ዘንድሮ የተከሰቱት አደጋዎች ካለፉት ዓመታት ጋር ሲነጻጸሩ በእጅጉ የቀነሱት ማኅበረሰቡን በማሳተፍ በተከናወኑ የመከላከል ሥራዎች መሆኑን አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅትም የበልግ ዝናብን ተከትሎ ሊከሰት የሚችለውን አደጋ ለመቀነስ ለናዳ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ አርሶ አደሮችን ለጊዜው ከአካባቢው የማውጣት ሥራ እየተሰራ ነው። በከተሞች በቆሻሻ የተደፈኑ የፍሳሽ ቦዮችን የማጽዳት ተግባር፤ ያልተጠበቀ የወንዝ ሙላት ለሰውና ለእንስሳት ሕይወት መጥፋት ምክንያት እንዳይሆን ማኅበረሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች እየሰሩ ነው ብለዋል። የደቡብ አሪ ወረዳ የወሰት ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ኃይሉ ከማይ በሰጡት አስተያየት፤ አካባቢያቸው ለናዳ ተጋላጭ መሆኑን በመገንዘብ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። አደጋ እንዳይደርስባቸውም ለጊዜው ከአካባቢው በመራቅ ራሳቸውን እየጠበቁ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሌላኛው የአስተያየት ሰጪ የባካ ዳውላ አሪ ወረዳ የሴኔጋል ቀበሌ ነዋሪ አቶ ማርቆስ አዲሱ በበኩላቸው፤ በአካባቢው በተከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ቀደም ሲል ይከሰት የነበረውን ናዳ መከላከል መቻላቸውን ገልጸዋል። ለናዳ ተጋላጭ በሆኑ ስፍራዎች ችግኞችን በመትከል አፈሩ እንዳይሸረሸር ጥበቃ እያደረግን ነው ያሉት አቶ ማርቆስ፤ በዚህም አደጋዎችን አስቀድሞ መከላከል መቻሉን አረጋግጠዋል።
አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ጨምሮ ለደን ልማት በተሰጠው ትኩረት የደን ሽፋን ጨምሯል
Mar 17, 2026 357
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ጨምሮ ለደን ልማት የተሰጠው ትኩረት ሀገራዊ የደን ሽፋኑ እንዲያድግ ማስቻሉን የኢትዮጵያ የደን ልማት አስታወቀ። የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር ከበደ ይማም መጋቢት 12 ቀን 2018 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚከበረውን 14ኛው የዓለም የደን ቀንን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ዳይሬክተሩ በመግለጫቸው፤ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የደን ጭፍጨፋ እንደነበር አስታውሰው፤ በዚህም የኢትዮጵያ የደን ሽፋን በዕጅጉ ቀንሶ እንደነበር አስረድተዋል። ለአብነትም ከአስር ዓመት በፊት በየዓመቱ ዘጠና ሁለት ሺህ ሄክታር መሬት ደን ይጨፍጨፍ ነበር ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ አሁን ላይ ወደ ሃያ ሰባት ሺህ ሄክታር ዝቅ እንዲል መደረጉን ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ጨምሮ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ለደን ልማት የተሰጠው ትኩረት በመስኩ ትልቅ ውጤት እንዲመጣ ማስቻሉን አብራርተዋል። ከሀገራዊ ለውጡ በፊት 17 ነጥብ 2 በመቶ የነበረው የደን ሽፋን አሁን ላይ ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ማለቱን ተናግረዋል። 14ኛው የዓለም የደን ቀንም በኢትዮጵያ በዘርፉ የተገኙ ስኬቶች ከማጉላት ባለፈ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት ይበልጥ በማጠናከር ለላቀ ውጤታማነት የሚመከርበት ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ የደን ሽፋን እያደገ መምጣቱን ተከትሎ በርካታ ውጤቶች እየተገኘ ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የውኃ አቅርቦት እንዲሻሻል፣ የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ ማስቻሉንም ገልጸዋል። ይህም ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ከማገዝ ባለፈ ብዝሃ ህይወት እንዲጠበቁ አወንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ብለዋል። በተለይም ሙቀት አማቂ ጋዞችን በመቀነስ ረገድ የኢትዮጵያ የደን ኃብት ከፍ ያለ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ስጋት የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል በሚደረገው ጥረትም ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተችና ለዚህ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተጠቃሽ ማሳያ ነው ብለዋል። 14ኛው የዓለም የደን ቀን "ደን ለኢኮኖሚ" በሚል መሪ ሀሳብ ይከበራል።
የአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ ልማት የአካባቢ ጥበቃን ከቱሪዝም ጋር በማስተሳሰር በአርዓያነት የሚጠቀስ ነው
Mar 16, 2026 227
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ ልማት ወንዞችን አረንጓዴ በማልበስና የአካባቢ ጥበቃን ከቱሪዝም ጋር በማስተሳሰር ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በአርዓያነት የሚወሰድ መሆኑን የዛምቤዚ ወንዝ ተፋሰስ ኮሚሽን አባላት ሀገራት ተወካዮች ገለፁ። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለዛምቤዚ ተፋሰስ አገራት ተሞክሮ የሚሆን ነው የዛምቤዚ ወንዝ ተፋሰስ ኮሚሽን አባል ሀገራት ተወካዮች የአዲስ አበባን የወንዝ ዳርቻ ልማት ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ወቅት የመዲናዋን የወንዞች ዳርቻ በማልማት ከቆሻሻ መጠራቀሚያነት አውጥቶ ወደ ሕዝብ መዝናኛነትና የከተማ ውበት አካል እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን አድንቀዋል። በተለይም የወንዝ ዳርቻዎችን አረንጓዴ በማልበስ የአካባቢ ጥበቃን ከቱሪዝም ጋር የማስተሳሰር ረገድ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ትልቅ ትምህርት እንደሚሆን ገልጸዋል። የዛምቤዚ ወንዝ ተፋሰስ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ፌሊክስ ሞሲ ንጋምላጎሲ፥ የአፍሪካ ከተሞች የታቀዱ፣ ሳቢ እና የቱሪስት መዳረሻዎች እንዲሆኑ በማድረግ ረገድ አዲስ አበባ በአርዓያነት የምትጥቀስ ናት ብለዋል። በተለይም አሁን ላይ በአዲስ አበባ እየታዩ ያሉ ለውጦች ከተማዋን ለሰዎች መዝናኛና ለኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ተመራጭ እያደረጓት መሆኑን ተናግረዋል። ሌሎች የአፍሪካ ከተሞች በአዲስ አበባ እየተከናወኑ ካሉ የልማትና የከተማ ውበት ስራዎች ልምድ እንዲቀስሙና ትምህርት እንዲወስዱ ጥሪ አቅርበዋል። ከዚምባብዌ የመጡት ቺቶ ፊሪ በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ የሕዝብ መዝናኛ ፓርኮች በስፋት ተገንብተው መመልከታቸውን በአድናቆት ጠቅሰዋል። ይህም ለከተማዋ ድምቀት ከመሆኑ ባለፈ ለነዋሪዎችና ለጎብኝዎች ምቹ የመንቀሳቀሻ ከባቢን የሚፈጥር ነው ብለዋል። በአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻና የኮሪደር ልማት ለእግረኛ መንገድ የተሰጠው ትኩረት ለጤና እጅግ ተስማሚ የሆነውን የእግር ጉዞ ባህል እንደገና ለማነቃቃት ትልቅ ዕድል መፍጠሩንም ነው የተናገሩት። ከሞዛቢክ የመጡት ማኑኤል ቻጉሎ፤ ከ15 ዓመታት በፊት ኢትዮጵያን ጎብኝተው እንደነበር በማስታወስ፤ አሁን ድጋሚ ሲመጡ አዲስ አበባ አስድናቂ ለውጥና ዕድገት አስመዝግባ እንዳገኟት ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት ልምድ የሚቀሰምበት ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቷን ጠቅሰዋል።