አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው - አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ
Mar 21, 2026 99
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለሌሎች ሀገራት ትልቅ መነሳሳትን የሚፈጥርና ምሳሌ የሚሆን ፕሮጀክት ነው ሲሉ በኢትዮጵያ የኮሎምቢያ አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የተጀመረው አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እስካሁን ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ተተክለዋል። ይህም የአካባቢ ጥበቃን ከማጠናከር ባለፈ፣ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ብዝሃ ህይወትን ለመጠበቅ ትልቅ ሚና እየተጫወተ ነው። ይህ መርሃ ግብር በአፍሪካ ቀዳሚ የሆነ ግዙፍ የደን ልማትና የተፈጥሮ ጥበቃ ዘመቻ ሲሆን የካርቦን ልቀትን በመቀነስ ረገድም በምሳሌነት ተጠቃሽ ነው። ሀገሪቱ የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም የተፈጥሮ ሥርዓት እንድትገነባ እያገዘም ይገኛል። በኢትዮጵያ የኮሎምቢያ አምባሳደር ዮሶን አርካዲዮ ሜኔስ ኮፔቴ ለኢዜአ በሰጡት ቃለ ምልልስ፣ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የሚመራው የአረንጓዴ አሻራ ፖሊሲ እጅግ የሚደነቅ ጥረት ነው ብለዋል። አረንጓዴ አሻራ ለሌሎች ሀገራትና መሪዎች አርአያ የሚሆን ተሞክሮ እንደሚሆን ጠቁመው ይህ ተግባር ሁላችንም በጋራ እንድንሰራ ያበረታታናል ነው ያሉት። የሀገራት መሪዎች በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት እየመጡ ያሉ ተግዳሮቶችን ለዜጎች በግልጽ ማሳወቅ እንዳለባቸውና ይህም ዜጎች ለመፍትሄው እንዲሰሩ ያደርጋል ሲሉ ገልጸዋል። በተጨማሪም ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2027 የሚካሄደውን 32ኛውን የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 32) እንድታስተናግድ መመረጧን አምባሳደሩ አድንቀዋል። ኮሎምቢያ እ.ኤ.አ. በ2024 የኮፕ 16 ጉባኤን ማስተናገዷን አውስተው ኢትዮጵያ ኮፕ 32ን በምታዘጋጅበት ወቅት ሀገራቸው ያካበተችውን ልምድ ለማካፈል ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል። አምባሳደሩ አክለውም የኮሎምቢያን ተሞክሮና የኢትዮጵያን የወደፊት ራዕይ በማጣመር፣ ተግዳሮቶችን በጋራ ለመፍታት ይሰራሉ ብለዋል።
የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ለሚያሻሽሉ መመሪያዎች ተፈፃሚነት ጥብቅ ቁጥጥር ይደረጋል
Mar 21, 2026 110
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ የሚያሻሽሉ መመሪያዎችን በማውጣት ለተግባራዊነታቸው ጥብቅ ቁጥጥር እንደሚደረግ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢዎችና የአካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ከፋርም አፍሪካና ኤስ.ኦ.ኤስ ሳህል ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በሥርዓተ ምህዳር አገልግሎት ክፍያ ትግበራ ላይ ትኩረት ያደረገ የውይይት መድረክ አካሂዷል፡፡ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የባለድርሻ ተቋማትን ትብብር በማጠናከር በደንብ ቁጥር 545/2016 በተሰጠው ኃላፊነት መሰረት የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ሥርዓትን ይከታተላል፤ ይቆጣጠራል፡፡ የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ተፈጥሮ የቸራትን ዕምቅ የብዝኅ ህይወት ሃብት በሚገባት ልክ ጥቅም ላይ እያዋለች እንዳልሆነ ገልጸዋል። ለዚህም የውሃና የየብስ የሥነ-ምኅዳር ጸጋዎች ለሀገር የኢኮኖሚ ጥቅም ለማዋል የሚስችል "የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ቁጥር 140/2018" ተግባራዊ መደረጉን አስታውቀዋል። ምክር ቤቱም ከመንግስተና የዘርፉ ተዋናዮች ጋር የግብዓት ማሰባሰቢያ መድረኮችን በማዘጋጀት ግብዓት ታክሎበት አዋጁን በማፅደቅ ሥራ ላይ እንዲውል መደረጉን ተናግረዋል። በዚህም የዜጎችን የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ለማሻሻል የሚረዱ የማስፈጸሚያ ደንቦችና መመሪያዎች መውጣታቸውንና ተፈፃሚነ መሆናቸውን ጥብቅ ክትትል እንደሚደረግ አንስተዋል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ንጉሱ ለማ፤ በሀገር አቀፍ ደረጃ የተቀናጀ የሥነ-ምህዳር አገልግሎት የክፍያና የሕግ ማዕቀፍ እንዳለነበረ ገልጸዋል፡፡ በዚህም የኢትዮጵያ ሥርዓተ ምኅዳር ዘላቂነት ለማስጠበቅ የመንግስትና የባለድርሻ ተቋማትን ፍላጎት ታሳቢ ያደረገ የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ቁጥር 140/2018 መፅደቁን ተናግረዋል። የአገልግሎት ክፍያ የአሰራር ሥርዓቱም የኢኮኖሚ ዕድልን በመፍጠርና ለአገልግሎቱ አቅራቢዎች ዘላቂ ዋስትናን ይፈጥራል ብለዋል፡፡ አዋጁን መነሻ በማድረግ የዘርፉን ተዋናዮች ተሳትፎ ማሳደግ የሚያስችል የማስተግበሪያ መመሪያ መዘጋጀቱን አስረድተዋል። የፋርም አፍሪካ የኢትዮጵያ ዳይሬክተር ሸዊት አማኑኤል፤ ኢትዮጵያ ደኖችን በመንከባከብ የበካይ ጋዝ ልቀትን በመቀነስ ለዓለም የከባቢ አየር ሥነ ምህዳር ገንቢ ሚና እየተወጣች መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያዊያን ደንን በመንከባከብ በአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ በሚበረክቱት አስተዋፅኦ ልክ ሳይንሳዊ ጥናትና ኦዲት ተካሂዶ ገቢ ማመንጨት መጀመሩን አንስተዋል። የሥርዓተ ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ በባሌ አካባቢ የተጀመረውን በሌሎች አካባቢዎች ለማስፋት በር የሚከፍት መልካመ ዕድል መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የደን ሽፋንን በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ ይገኛል
Mar 21, 2026 79
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን የደን ሽፋን በማሳደግ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከተ እንደሚገኝ የግብርና ሚኒስትር አዲሱ አረጋ ገለጹ። የፌዴራልና የክልል መንግስታት የግብርና ዘርፍ የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት ''የመደመር መንግሥት የተፈጥሮ ሃብት ዕይታ'' በሚል መሪ ሃሳብ የዓለም አቀፍ የደን ቀን የምክክር መድረክ ተካሂዷል፡፡ በመድረኩ የግብርና ሚኒስትር አቶ አዲስ አረጋ፤ የመደመር መንግሥት ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሰጠው ትኩረት የተፈጥሮ ሃብቶችን በማስጠበቅ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ማበርከት ያስቻለ ውጤት መገኘቱን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት ስምንት የለውጥ ዓመታት ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል የኢትዮጵያን የደን ሽፋን ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ማሳደግ እንደተቻለ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የተራቆተ የመሬት ገፅታ በደን በመሸፈን የአፈር መሸርሸርና የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን መጠበቅ ያስቻለ ውጤት እየተገኘ መሆኑንም አንስተዋል። ቡናን ጨምሮ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞች የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያበረከቱ እንደሚገኝ አብራርተዋል። በቀጣይም የማህበረሰቡን የደን ጥበቃ ግንዛቤ በማሳደግና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በማስቀጠል በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርና የደን ልማት ስኬትም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቀነስ የግብርና ምርታማነትን እያሳደገ እንደሚገኝ አብራርተዋል። ለአብነትም ከሰባት ዓመታት በፊት ወደ ውጭ ይላክ የነበረን 230 ሺህ ቶን የቡና ምርት አሁን ላይ ወደ 475 ሺህ ቶን በማሳደግ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ ማግኘት እንደተቻለ አንስተዋል። የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር ከበደ ይማም በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ የደን ሃብት ልማት መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እያስገኘ ነው ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በ2011 ዓ.ም የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ስኬታማነትም ከክልልና ባለድርሻ ተቋማት ጋር በቅንጅት መሰራቱን አንስተዋል። የአረጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የቴክኒክ ኮሚቴ አስተባባሪ አደፍርስ ወርቁ (ዶ/ር)፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ያስገኘውን ስኬትና ቀጣይ ሥራ የሚዳስስ የመነሻ ጽሁፍ አቅርበዋል። ይህም የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የዓባይ ተፋሰስ ወረዳዎችን የተራቆተ የመሬት ገፅታ በደን በመሸፈን የከርሰና የገፀ ምድር ሃብቶች ላይ ዘርፍ ብዙ ጠቀሜታ እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል።
የተፈጥሮ ሃብት አገልግሎት አቅራቢዎች ለሥነ-ምኅዳር ደኅንነት በይበልጥ ሊተጉ ይገባል
Mar 21, 2026 79
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 12/2018 (ኢዜአ)፡- የተፈጥሮ ሃብት አገልግሎት አቅራቢዎች የአካባቢ ጥበቃ ባህልን በማሳደግ ለሥነ-ምኅዳር ደኅንነት ይበልጥ ሊሠሩ እንደሚገባ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን አሳሰበ። ባለሥልጣኑ ከፋርም አፍሪካ እና ኤስ.ኦ.ኤስ ሳህል ኢትዮጵያ ጋር በመተባበር በሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ትግበራ ላይ ትኩረት ያደረገ የውይይት መድረክ እያካሄደ ነው። በዚሁ ወቅትም የባለሥልጣኑ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ንጉሡ ለማ፤ ተቋማቸው የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ ሥርዓትን የመከታተልና የመቆጣጠር ኃላፊነት እንዳለበት ገልጸዋል። በዚህም የኢትዮጵያን ሥርዓተ-ምኅዳር ዘላቂነት ለማስጠበቅ የመንግሥትና የባለድርሻ ተቋማትን ፍላጎት ታሳቢ ያደረገ የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት ክፍያ አዋጅ ቁጥር 140/2018 መጽደቁን አስረድተዋል። የሥርዓተ-ምኅዳር የአገልግሎት ክፍያ የአሠራር ሥርዓቱም ለተጠቃሚዎችና አገልግሎት አቅራቢዎች ምቹ የክፍያ መፈጸሚያ ሁኔታ እንደፈጠረ አረጋግጠዋል። ይህም የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎት አቅርቦትን በማሻሻልና ዘላቂነት እንዲኖረው ከፍተኛ እገዛ ያደርጋል ብለዋል። አዋጁም ከዚህ በፊት ክፍያ ያልተተመነላቸው የሥርዓተ-ምኅዳር አገልግሎቶች ላይ የዋጋ ተመን በማስቀመጥ የኢኮኖሚ ዕድልን እንደሚፈጥር አስረድተዋል። ለአዋጁ ገቢራዊነት የዘርፉ ተዋንያን ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ባለሥልጣኑ ለአዋጁ ማስፈጸሚያነት የሚየገለግሉ መመሪያዎች ማዘጋጀቱን አስታውቀዋል።
ለነዋሪዎቿ ምቾትን የፈጠረው የአዲስ አበባ አዲሱ ገጽታ
Mar 19, 2026 135
አዲስ አበባ እየተዋበች፤ እየደመቀች ነው። ለተሽከርካሪዎች ብቻ ሳይሆን ለእግረኞችም ምቹና ሰፋፊ ጎዳና ገንብታለች። ይህን የስልጡንነት አክሊል የተቀዳጀችው ይህች መዲና ልክ እንደ ስሟ መልክና ግብሯ አጊጧል። ዛሬ ላይ የመዲናዋ አውራ ጎዳናዎች በግራና በቀኝ በእግረኛ መንገዶች የታጀቡ ናቸው። በእግሩ የሚጓዝ ነዋሪም ይሆን ጎብኚ በመዲናዋ ዞር ዞር ቢል የከተማነትን ክብርና የሰው ልጅን ነጻነት የሚያውጅ አዲስ የከተማ ልማትን በተግባር ይመለከታል። ለወትሮው በጠባብ የእግረኛ መንገዶች፣ ለትራፊክ በማይመቹ አውራ ጎዳናዎች ትታወቅ የነበረችው መዲና፣ ዛሬ በኮሪደር ልማት አማካኝነት መልኳን እየቀየረች ትገኛለች። ይህ ልማት የከተማዋን ውበት ከማድመቅ ባለፈ፣ የነዋሪዎቿን የዕለት ተዕለት ሕይወት ምቹ፣ ቀላልና ስሉጥ አድርጎታል። በመዲናዋ የከተማ አኗኗርና የመንገድ አጠቃቀም ባህልም እየተቀየረ መሆኑን ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች ይገልጻሉ። በመዲናዋ ቀደም ባሉት ጊዜያት በእግር ለመጓዝ ምቹ መንገድ ባለመኖሩ ጉዞው አድካሚና አሰልቺ ነበር። ዛሬ ግን ሁኔታዎች ተቀይረዋልም ነው ያሉት። ይህም የእግር ጉዞን ማድረግ ያለውን የጤና ገፀበረከት እንድንቋደስ እያደረገን ነው ብለዋል በእግራቸው ሲጓዙ ያገኘናቸው ነዋሪዎች። የከተማዋ ነዋሪ የሆኑት ነጋ ፍቅሬ እንደሚሉት፣ የኮሪደር ልማቱ አዲስ አበባን ለእግረኞችና ብስክሌት ለሚጠቀሙ ተጓዦች ምቹ አድርጓታል። መንገዶቹ ለእግር ጉዞ እጅግ ምቹ ናቸው፤ በቀላሉ ለመንቀሳቀስና ለመዝናናትም አማራጭ ሆነዋል፤ ያሉት አቶ ነጋ ከቦታ ቦታ መንቀሳቀሻነት ባለፈ በየዳርቻቸው ለዓይን የሚማርኩ ሥፍራዎችን ያካተቱ መሆናቸውን አንስተዋል። የአዲስ አበባ ልማት ስኬት ግን ከዚህም በላይ ነው፤ በአካታችነቱ የሚወደሥ ተጨባጭ ለውጥ በመዲናዋ ጎላ ብሎ ይታያል። መምህር ጌታ ጫኔ ማየት የተሳናቸው ናቸው። ለእርሳቸው በመዲናዋ በእግር ከቦታ ቦታ መጓዝ ቀደም ሲል ትልቅ ፈተናና ስጋት ነበር። የኮሪደር ልማት ግን የእርሳቸውንና መሰል አካል ጉዳተኛ ዜጎችን ፍላጎት ታሳቢ ያደረጉ መንገዶችን እውን አድርጓል። ይህም በተለይ ለዓይነ ሥውራን የህብረተሰብ ክፍሎች ትልቅ እፎይታን የፈጠረ ነው። መምህር ጌታም ይህንኑ በማጠናከር ይህ ልማት ለእኛ ትልቅ ትርጉም አለው። የአካል ጉዳተኞችን ተጠቃሚነት ያረጋገጠ፣ በምቾት ሳንሳቀቅ እንድንቀሳቀስ ያስቻለንና ትልቅ የመንገድ ደህንነት ስጋታችንን የቀረፈ ስራ ነው ብለዋል። በሌላ በኩል የኮሪደር ልማቱ መዲናዋን ወደ ተሻለ የዕድገት ምዕራፍ እንዳሸጋገራት የሚናገሩት ወይዘሮ መንበረ አግዘው ናቸው። አዲስ አበባ አሁን ለመኖርም ሆነ ለመዝናናት ተመራጭ መዲና ሆናለች ይላሉ። አቶ ዘሩ ተገኝ በበኩላቸው የተዘረጋው መሠረተ ልማት ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል ታሳቢ ያደረገ መሆኑ አዲስ አበባ ለነዋሪዎቿ ምቹና ሰው ተኮር ልማቶች የሚከናወኑባት ከተማ እንድትሆን አድርጓታል ይላሉ። የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት የአፍሪካ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን በሚመጥን መልኩ ገፅታዋን ከመቀየር ባለፈ፣ ለአካል ጉዳተኞች ደህንነቱ የተጠበቀ መንገድ፣ የእግር ጉዞ ለሚያዘወትሩ ደግሞ ሰፊና ማራኪ ጎዳናን ፈጥሯል።
የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በዜጎች አኗኗር እና ጤና ላይ መሰረታዊ ለውጥ እያመጣ ነው
Mar 19, 2026 189
ወልቂጤ፤መጋቢት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በዜጎች አኗኗር እና ጤና ላይ መሰረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑን የጤና ዘርፍ የስራ ሃላፊዎች ገለጹ። አዋጁ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግብ ለማድረስ ያግዛል የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ በሀገሪቱ የቆሻሻ አወጋገድ ስርዓትን ለማሻሻል፣ የከተሞችን ውበት ለመጠበቅ እና ለዜጎች ምቹ የመኖሪያ አካባቢን ለመፍጠር ያለመ ሀገራዊ ዘመቻ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነት የተጀመረው ኢንሼቲቭ በሁሉም የሀገሪቷ አካባቢዎች ተግባራዊ እየተየደረገ ያለ መሆኑ ይታወቃል። የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ዋነኛ ዓላማም በተለይም በከተሞች የሚታየውን የንፅህና ጉድለት በማስተካከል ለነዋሪዎችና ለጎብኝዎች ዘመናዊና ምቹ ከተሞችን የመፍጠር ነው። በዚህም መሰረት የተገነቡ መሠረተ ልማቶችን በአግባቡ መጠገንና መጠበቅ፣ የቆሻሻ አወጋገድን የማዘመን፤ የመፀዳጃ ቤቶችን የማስፋትና የማዘመን ስራ በስፋትና በጥራት ማከናወን ተችሏል። ከዚህ አንፃር በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በፅዱ ኢትዮጵያ ኢንሼቲቭ የተገኘውን ውጤት በተመለከተ የኢዜአ ሪፖርተር የጤና ዘርፍ ሃላፊዎችንና ነዋሪዎችን አነጋግሯል። የጉራጌ ዞን ጤና መምሪያ ሃላፊ አየለ ፈቀደ፤ በኢንሼቲቩ በገጠርም ይሁን በከተሞች ሰፊ ተግባራት መከናወናቸውን ገልጸው ለስኬቱ በየደረጃው ያሉ የስራ ሃላፊዎችና አጠቃላይ የማህበረሰቡ ተሳትፎ የላቀ መሆኑን ገልጸዋል። ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ብዙ ተያያዥ የሆኑ ማህበራዊና የምጣኔ ሃብት ጥቅሞች እያስገኘ መሆኑን የገለጹት ሃላፊው በቀጣይም በተጠናከረ መልኩ ይቀጥላል ብለዋል። የአካባቢ ጽዳትና ውበትን በጋራ በመጠበቅና በመንከባከብ ምቹና ተመራጭ አካባቢ ለመፍጠር ዜጎችን በማሳተፍ ስኬት እየተመዘገበ ነው ብለዋል። በሁሉም የዞኑ አካባቢዎች ፅዱ እና ለመኖርያነት ምቹ የሆኑ መንደሮች እንዲሁም ሜዳ ላይ ከመፀዳዳት ነፃ የሆነ አካባቢ ለመፍጠር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። እስካሁን በዞኑ ከሚገኙ 315 ቀበሌዎች መካከል 70 በመቶ ያህሉ የዚህ ኢንሼቲቭ ትግበራ ተጠቃሚዎች መሆን መቻላቸውንም ለአብነት አንስተዋል። የሃድያ ዞን ጤና መምሪያ ሃላፊ ዶ/ር ደሳለኝ ሽጉጤ፤ የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በየአካባቢው ካለው ማህበረሰብ ባለፈ ከጤና፣ ከትምህርት እና ከሃይማኖት ተቋማት ጋር በቅንጅት መሰራቱ ውጤት አምጥቷል ብለዋል። የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በዞኑ ህዝብ ጤና እና አኗኗር ላይ ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ በመሆኑ ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ተናግረዋል። የምስራቅ ጉራጌ ዞን ጤና መምሪያ ሃላፊ ሰለሞን ጉግሳ፤ የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በዞኑ በርካታ ቀበሌዎች እና ወረዳዎችን ጽዱ አካባቢ ማድረግ አስችሏል ብለዋል። የማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ሃላፊ ሳሙኤል ዳርጌ፤ የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በክልሉ መሰረታዊ የሚባል ውጤት የመጣበት ስኬታማ ትግበራ መሆኑን ገልጸዋል። መርሃ ግብሩ የተሻሻሉ መፀዳጃ ቤት በመገንባት የሰውና እንስሳ መኖርያ በመለየት ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር እያስቻለ ነው ብለዋል። በመሆኑም የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በክልሉ ዜጎች አኗኗር እና ጤና ላይ መሰረታዊ ለውጥ እያመጣ መሆኑን አንስተው ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል። በጉራጌ ዞን የተለያዩ ወረዳዎች ነዋሪዎችም የፅዱ አካባቢ ልማት በቆሻሻ አወጋገድና አጠቃቀም ላይ መሰረታዊ ለውጥ ማምጣቱን ተናግረዋል።
ለሀገራዊ የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ ትግበራ የባለድርሻ አካላት ቅንጅት መጠናከር አለበት
Mar 18, 2026 155
አዲስ አበባ፤መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ ስኬታማ ለማድረግ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎና ቅንጅት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ገለጹ። ባለስልጣኑ የፍኖተ ካርታውን ትግበራ ውጤታማ ለማድረግ ከተለያዩ የፌዴራል ተቋማት ጋር በጋራ መስራት የሚያስችል የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ(ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ባለስልጣኑ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል፡፡ በዚህም ፅዱ ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ለውጥ የሚያመጡ የህግና አሰራር ስርዓት ወደ ተግባር በማስገባት ለሌሎች ሀገሮች ምሳሌ የሚሆኑ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ገልፀዋል። የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ልማት ግቦችን ለማሳካትና ወደ ሰርኩላር ኢኮኖሚ የሚደረገውን ሽግግር ማፋጠን የሚያስችለው ሀገራዊ ፍኖተ ካርታ በ2017 ዓ.ም ተዘጋጅቶ ወደ ትግበራ መገባቱን አስታውሰዋል። ፍኖተ ካርታው ፅዱ ኢትዮጵያን በመፍጠር ሂደት ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ የማዋል(Recycling) ባህልን የሚያበረታታ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን በማጎልበት፣ ለተሻለ ኢንቨስትመንት ምቹ ሁኔታን በመፍጠርና አዳዲስ የስራ እድሎችን በመክፈት የሀገርን ኢኮኖሚ ለማሳደግ ጉልህ ሚና ይጫወታል ብለዋል። የአካባቢ ጥበቃ ስራ በአንድ ተቋም ብቻ ውጤታማ ማድረግ ስለማይቻል የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት እንደሚጠይቅ ጠቅሰዋል። በዚህም ወደ ሰርኩላር ኢኮኖሚ የሚደረገው ሽግግር እንዲፋጠን ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቁርጠኝነትና በተጠናከረ ተሳትፎ የበኩላቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። ከተቋማቱ ጋር የተደረገው ስምምነት በአካባቢ ጥበቃ ስራዎች ላይ ሰፊ የግንዛቤ ማስጨበጫ ተግባራትን ማከናወን፣ የህግና አሰራር ማሻሻያዎች፣ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ስርዓትን በቴክኖሎጂና በዕውቀት መደገፍ እንዲሁም የጋራ የድጋፍና ክትትል ስራዎችን በቅንጅት መስራት ከሚከናወኑ ሥራዎች መካከል ናቸው ብለዋል፡፡ ስምምነቱን ከተፈራረሙ ተቋማት መካከል የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን እንደገለጹት በባለስልጣኑ የተዘጋጀው ፍኖተ ካርታ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ ትልቅ ፋይዳ አለው፡፡ በሀገሪቱ የሚከናወኑ ግንባታዎች በመልሶ መጠቀም የተዘጋጁ የሀገር ውስጥ ግብዓቶችን እንዲጠቀሙ በትኩረት እንደሚሰራ ተናግረዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትር ዴኤታ ሃሰን መሃመድ በበኩላቸው የተዘጋጀው ፍኖተ ካርታ ከኢንዱስትሪ ዘርፉ ፖሊሲ ጋር የሚቀናጅ በመሆኑ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት ይሰራል ብለዋል። የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አለበል ደሴ በበኩላቸው ኢንስቲትዩቱ የፖሊሲ ፋይዳ ያላቸው ሀገራዊ ጥናቶችን በመለየት ፖሊሲ አውጪውን የማማከር ስራ የሚሰራ ተቋም እንደመሆኑ ለፍኖተ ካርታው ትግበራ በትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ደረጃዎች ኢንስቲትዩት የዋና ዳይሬክተር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ሳባ ዘሪሁን በበኩላቸው በዚህ ስራ ባለድርሻ እንደመሆናችን የበኩላችንን አስተዋጽኦ ለማበርከት ዝግጁ ነን ብለዋል።
የአዲስ አበባ ኮሪደርና የአረንጓዴ ልማት ስኬቶች ለአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ዕድገት ትምህርት የሚሰጥ ነው
Mar 18, 2026 137
አዲስ አበባ፤መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ ኮሪደርና የአረንጓዴ ልማት ስኬቶች ለአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ዕድገት ትምህርት የሚሰጥ መሆኑን የዛምቢያና ኢስዋቲኒ የአካባቢ ጥበቃ ሙያተኞች ገለጹ። በአዲስ አበባ የተገነቡ የኮሪደርና የወንዝ ዳርቻ ልማት ሥራ መዲናዋን ውብ ገፅታ በማላበስ ለነዋሪዎችና ጎብኝዎች ምቹ የእንቅስቃሴ ምኅደር ፈጥረዋል። በመዲናዋ በአጭር ጊዜ የተመዘገቡ የልማት ውጤቶችም አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ዕውቅናን በማስገኘት ልምድና ተሞክሮ እየተቀሰመባቸው ይገኛል። በአዲስ አበባ የተጀመረው የኮሪደር ልማትም ከተማዋን ውብ ገፅታ በማላበስ ነዋሪዎችን ምቹና የአረንጓዴ ከባቢ በማጎናጸፍ በ75 የኢትዮጵያ ከተሞች እየተተገበረ ይገኛል። የዛምቢያና የኢስዋቲኒ የአካባቢ ጥበቃ ሙያተኞች ለኢዜአ እንዳሉት፤ አዲስ አበባ ከተማ የአፍሪካዊያን ማዕከልነቷን በተግባር ያረጋገጡ የልማት ውጤቶች ተገኝተዋል። በመዲናዋ በአጭር ጊዜ የተገነቡ አስደናቂ የልማት ውጤቶችም ከተማዋን ውብ ገፅታ በማላበስ ምቹ የከተሜነት ምኅዳር እንዲፈጠር ማድረጉን ገልጸዋል። በዛምቢያ የአካባቢና የገጠር ልማት ሚኒስቴር የደረቅ ቆሻሻ አስተዳደር ባለሙያ ብሬን ሲያካበያ፤ አዲስ አበባ ከጥቂት ዓመታት በፊት የተጎሳቆለና እርጅና የተጫጫነው ገፅታ እንደነበራት አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት በአጭር ጊዜ ውስጥ በአዲስ አበባ የተገነባው የኮሪደር ልማት ነዋሪዎች ምቹና ፅዱ የአረንጓዴ ከባቢን ያጎናጸፈ አስደናቂ ለውጥ መምጣቱን ገልጸዋል። የመዲናዋ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችና ሰማይ ጠቀስ ህንፃዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውም ውብ የከተሜነት ገፅታን በመፍጠር ልዩ ድምቀት እንደፈጠሩ ተናግረዋል። በህዝብና በአመራር ቁርጠኝነት ተገንብተው የተጠናቀቁት የአዲስ አበባ የልማት ስኬቶችም ሀገራቸውን ጨምሮ ለአፍሪካ ሀገራት ከተሞች ዕድገት ትልቅ ትምህርት መሆኑን አንስተዋል። የኢስዋቲኒ የአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ የኢኮኖሚ ባለሙያ መሎሰም ቡሊ በበኩላቸው፣ ከተሜነት የአንድ ሀገር የዕድገትና ስልጣኔ መገለጫ ነው ብለዋል። በአዲስ አበባ በአጭር ጊዜ የተገኙ ተምሳሌታዊ የኮሪደርና የአረንጓዴ ልማት ስኬቶች ዜጎች ዘመናዊ የከተሜነት አኗኗር ሥርዓት እንዲጎናጸፉ ያደረጉ መሆናቸውን ገልጸዋል። የመዲናዋ አስደናቂ የከተማ ውበት፣የአረንጓዴና ቆሻሻ አያያዝ የልማት ስኬቶች የአፍሪካን የአየር ንብረት ለውጥና የአካባቢ መራቆት የመቀነስ ግብ ያገናዘቡ መሆናቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ልማትም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን በመቀነስ አህጉራዊ አጀንዳዎችን የሚያሳካና ትምህርት የሚቀሰምበት መሆኑን አንስተዋል።
በአሪ ዞን ማኅበረሰቡን ያሳተፈ የጎርፍ እና የናዳ ቅድመ መከላከል ሥራ እየተከናወነ ነው
Mar 18, 2026 183
ጂንካ፤ መጋቢት 9/2018 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አሪ ዞን ለጎርፍ እና ለናዳ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ማኅበረሰቡን በማሳተፍ አደጋን ቅድመ የመከላከል ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ አደጋ ሥጋትና ሥራ አመራር ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። የዞኑ አደጋ ሥጋትና ሥራ አመራር ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አስራት አበበ እንደገለጹት፤ በአሪ ዞን የሚገኙ አራት ወረዳዎች በመልክዓ ምድራዊ አቀማመጣቸው ተራራማና ተዳፋት በመሆናቸው በተደጋጋሚ ለናዳ አደጋ ተጋላጭ ናቸው። በተመሳሳይ በዞኑ የሚገኙ ሦስት ከተሞች ደግሞ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ባለፈው ዓመት ወቅት በዎባ አሪ ወረዳ በተከሰተ የአፈር መንሸራተት በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት መድረሱን ያስታወሱት ኃላፊው፤ በዘንድሮው ዓመትም በደቡብ አሪ ወረዳ ወሰት ቀበሌ መሰል አደጋ መከሰቱን ተናግረዋል። ዘንድሮ የተከሰቱት አደጋዎች ካለፉት ዓመታት ጋር ሲነጻጸሩ በእጅጉ የቀነሱት ማኅበረሰቡን በማሳተፍ በተከናወኑ የመከላከል ሥራዎች መሆኑን አስረድተዋል። በአሁኑ ወቅትም የበልግ ዝናብን ተከትሎ ሊከሰት የሚችለውን አደጋ ለመቀነስ ለናዳ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ አርሶ አደሮችን ለጊዜው ከአካባቢው የማውጣት ሥራ እየተሰራ ነው። በከተሞች በቆሻሻ የተደፈኑ የፍሳሽ ቦዮችን የማጽዳት ተግባር፤ ያልተጠበቀ የወንዝ ሙላት ለሰውና ለእንስሳት ሕይወት መጥፋት ምክንያት እንዳይሆን ማኅበረሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች እየሰሩ ነው ብለዋል። የደቡብ አሪ ወረዳ የወሰት ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አቶ ኃይሉ ከማይ በሰጡት አስተያየት፤ አካባቢያቸው ለናዳ ተጋላጭ መሆኑን በመገንዘብ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል። አደጋ እንዳይደርስባቸውም ለጊዜው ከአካባቢው በመራቅ ራሳቸውን እየጠበቁ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ሌላኛው የአስተያየት ሰጪ የባካ ዳውላ አሪ ወረዳ የሴኔጋል ቀበሌ ነዋሪ አቶ ማርቆስ አዲሱ በበኩላቸው፤ በአካባቢው በተከናወነው የተፋሰስ ልማት ሥራ ቀደም ሲል ይከሰት የነበረውን ናዳ መከላከል መቻላቸውን ገልጸዋል። ለናዳ ተጋላጭ በሆኑ ስፍራዎች ችግኞችን በመትከል አፈሩ እንዳይሸረሸር ጥበቃ እያደረግን ነው ያሉት አቶ ማርቆስ፤ በዚህም አደጋዎችን አስቀድሞ መከላከል መቻሉን አረጋግጠዋል።
አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ጨምሮ ለደን ልማት በተሰጠው ትኩረት የደን ሽፋን ጨምሯል
Mar 17, 2026 328
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 8/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ጨምሮ ለደን ልማት የተሰጠው ትኩረት ሀገራዊ የደን ሽፋኑ እንዲያድግ ማስቻሉን የኢትዮጵያ የደን ልማት አስታወቀ። የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር ከበደ ይማም መጋቢት 12 ቀን 2018 ዓ.ም በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚከበረውን 14ኛው የዓለም የደን ቀንን አስመልክቶ መግለጫ ሰጥተዋል። ዋና ዳይሬክተሩ በመግለጫቸው፤ በኢትዮጵያ ከፍተኛ የደን ጭፍጨፋ እንደነበር አስታውሰው፤ በዚህም የኢትዮጵያ የደን ሽፋን በዕጅጉ ቀንሶ እንደነበር አስረድተዋል። ለአብነትም ከአስር ዓመት በፊት በየዓመቱ ዘጠና ሁለት ሺህ ሄክታር መሬት ደን ይጨፍጨፍ ነበር ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ አሁን ላይ ወደ ሃያ ሰባት ሺህ ሄክታር ዝቅ እንዲል መደረጉን ተናግረዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ጨምሮ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ለደን ልማት የተሰጠው ትኩረት በመስኩ ትልቅ ውጤት እንዲመጣ ማስቻሉን አብራርተዋል። ከሀገራዊ ለውጡ በፊት 17 ነጥብ 2 በመቶ የነበረው የደን ሽፋን አሁን ላይ ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ማለቱን ተናግረዋል። 14ኛው የዓለም የደን ቀንም በኢትዮጵያ በዘርፉ የተገኙ ስኬቶች ከማጉላት ባለፈ የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት ይበልጥ በማጠናከር ለላቀ ውጤታማነት የሚመከርበት ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ የደን ሽፋን እያደገ መምጣቱን ተከትሎ በርካታ ውጤቶች እየተገኘ ነው ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ፤ የውኃ አቅርቦት እንዲሻሻል፣ የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙ ማስቻሉንም ገልጸዋል። ይህም ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ከማገዝ ባለፈ ብዝሃ ህይወት እንዲጠበቁ አወንታዊ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ብለዋል። በተለይም ሙቀት አማቂ ጋዞችን በመቀነስ ረገድ የኢትዮጵያ የደን ኃብት ከፍ ያለ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ስጋት የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል በሚደረገው ጥረትም ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወተችና ለዚህ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተጠቃሽ ማሳያ ነው ብለዋል። 14ኛው የዓለም የደን ቀን "ደን ለኢኮኖሚ" በሚል መሪ ሀሳብ ይከበራል።
የአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ ልማት የአካባቢ ጥበቃን ከቱሪዝም ጋር በማስተሳሰር በአርዓያነት የሚጠቀስ ነው
Mar 16, 2026 183
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፦የአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ ልማት ወንዞችን አረንጓዴ በማልበስና የአካባቢ ጥበቃን ከቱሪዝም ጋር በማስተሳሰር ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በአርዓያነት የሚወሰድ መሆኑን የዛምቤዚ ወንዝ ተፋሰስ ኮሚሽን አባላት ሀገራት ተወካዮች ገለፁ። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለዛምቤዚ ተፋሰስ አገራት ተሞክሮ የሚሆን ነው የዛምቤዚ ወንዝ ተፋሰስ ኮሚሽን አባል ሀገራት ተወካዮች የአዲስ አበባን የወንዝ ዳርቻ ልማት ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ወቅት የመዲናዋን የወንዞች ዳርቻ በማልማት ከቆሻሻ መጠራቀሚያነት አውጥቶ ወደ ሕዝብ መዝናኛነትና የከተማ ውበት አካል እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑን አድንቀዋል። በተለይም የወንዝ ዳርቻዎችን አረንጓዴ በማልበስ የአካባቢ ጥበቃን ከቱሪዝም ጋር የማስተሳሰር ረገድ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ትልቅ ትምህርት እንደሚሆን ገልጸዋል። የዛምቤዚ ወንዝ ተፋሰስ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ፌሊክስ ሞሲ ንጋምላጎሲ፥ የአፍሪካ ከተሞች የታቀዱ፣ ሳቢ እና የቱሪስት መዳረሻዎች እንዲሆኑ በማድረግ ረገድ አዲስ አበባ በአርዓያነት የምትጥቀስ ናት ብለዋል። በተለይም አሁን ላይ በአዲስ አበባ እየታዩ ያሉ ለውጦች ከተማዋን ለሰዎች መዝናኛና ለኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ተመራጭ እያደረጓት መሆኑን ተናግረዋል። ሌሎች የአፍሪካ ከተሞች በአዲስ አበባ እየተከናወኑ ካሉ የልማትና የከተማ ውበት ስራዎች ልምድ እንዲቀስሙና ትምህርት እንዲወስዱ ጥሪ አቅርበዋል። ከዚምባብዌ የመጡት ቺቶ ፊሪ በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ የሕዝብ መዝናኛ ፓርኮች በስፋት ተገንብተው መመልከታቸውን በአድናቆት ጠቅሰዋል። ይህም ለከተማዋ ድምቀት ከመሆኑ ባለፈ ለነዋሪዎችና ለጎብኝዎች ምቹ የመንቀሳቀሻ ከባቢን የሚፈጥር ነው ብለዋል። በአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻና የኮሪደር ልማት ለእግረኛ መንገድ የተሰጠው ትኩረት ለጤና እጅግ ተስማሚ የሆነውን የእግር ጉዞ ባህል እንደገና ለማነቃቃት ትልቅ ዕድል መፍጠሩንም ነው የተናገሩት። ከሞዛቢክ የመጡት ማኑኤል ቻጉሎ፤ ከ15 ዓመታት በፊት ኢትዮጵያን ጎብኝተው እንደነበር በማስታወስ፤ አሁን ድጋሚ ሲመጡ አዲስ አበባ አስድናቂ ለውጥና ዕድገት አስመዝግባ እንዳገኟት ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት ልምድ የሚቀሰምበት ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቷን ጠቅሰዋል።
የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለዛምቤዚ ተፋሰስ አገራት ተሞክሮ የሚሆን ነው
Mar 16, 2026 194
አዲስ አበባ፤መጋቢት 7/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎችን በማስተባበር ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የምታከናውነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለዛምቤዚ ተፋሰስ አገራት ትልቅ ተሞክሮ እንደሚሆን ተገለጸ፡፡ ለዛምቤዚ ወንዝ ተፋሰስ ኮሚሽን የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ ተሞክሮ ማጋሪያ መድረክ እየተካሄደ ነው። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ጥበቃ ዙሪያ የምታወራውን በተግባር የምትፈጽም አገር መሆኗን አስመስክራለች። ባለፉት ዓመታት የተተከሉ 48 ቢሊዮን ችግኞች ስኬት ምንጩ የአመራሩና የሕዝቡ ቁርጠኝነት መሆኑን ጠቅሰው መርሃ-ግብሩ ለቀጣዩ ትውልድ ብልጽግና ጠንካራ መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል። የኮሚሽኑ አባላት በኢትዮጵያ ቆይታቸው እነዚህን ተጨባጭ ልምዶች ወደ አገራቸው ይዘው እንደሚሄዱና ኢትዮጵያም ከሌሎች አገራት ልምድ ለመጋራት ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል። የዛምቤዚ ወንዝ ተፋሰስ ኮሚሽን ዋና ጸሐፊ ፌሊክስ ሞሲ ንጋምላጎሲ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በተፈጥሮ ላይ የተመሠረቱ መፍትሔዎችን በመተግበር ረገድ ያላትን አህጉራዊ መሪነት በተግባር ማሳየቷን ገልጸዋል። በተለይም ህዝብን በማስተባበር ረገድ የታየው ስኬት ለዛምቤዚ ተፋሰስ አገራት ትልቅ ትምህርት እንደሚሆን ጠቁመዋል። ዋና ጸሐፊው አያይዘውም ኢትዮጵያ በግዙፍ መሠረተ ልማቶች ያስመዘገበችውን ስኬት አድንቀዋል፡፡ ኢትዮጵያ እንደ ታላቁ የህዳሴ ግድብ፣ ግቤ 3 እና ኮይሻ ባሉ ፕሮጀክቶች የኃይል ዋስትናንና የኢኮኖሚ ዕድገትን ማረጋገጥ እንደሚቻል ለአፍሪካ በተግባር አሳይታለች ብለዋል፡፡ በዛምቤዚ ተፋሰስ ውስጥ እንደ ካሪባ እና ካቦራ ባሳ ያሉ ግድቦች ቢኖሩም፣ አሁንም ጥቅም ላይ ያልዋለ ሰፊ የውኃ ሀብት መኖሩን የጠቀሱት ዋና ጸሐፊው፤ የኢትዮጵያ ታላላቅ የመሠረተ ልማት ተሞክሮዎች ለተፋሰሱ አገራት ትልቅ መነሳሻ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
ለ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የላቀ ሀገራዊ ራዕይን በሚያሳካ መልኩ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Mar 15, 2026 281
አዲስ አበባ፤መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፡-ለ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የላቀ ሀገራዊ ራዕይን በሚያሳካ መልኩ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተጀመረ ሲሆን፤ መርሃ ግብሩ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ተተክሏል፡፡ በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈፃሚ ፋኖሴ መኮንን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለዘንድሮው መርሃ ግብር የመጀመሪያ ዙር የችግኝ ዝግጅት ተጠናቋል። ለስኬታማነቱም በርካታ ቁልፍ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመው፤ ሰባት ነጥብ አምስት ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል የሚያስችል ዕቅድ መዘጋጀቱን አብራርተዋል። በዚህም እስካሁን ከስድስት ቢሊዮን በላይ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ከችግኞቹ መካከልም 40 በመቶው ሀገር በቀል የደን ችግኞች ሲሆኑ፤ ቀሪው 60 በመቶው ደግሞ እንደ ፍራፍሬ እና የእንስሳት መኖ ያሉ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው ናቸው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በሀገር አቀፍ ደረጃ 110 ሺህ የችግኝ ጣቢያዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመዋል፡፡ የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ መሆኑ ጠቅሰው፤ ከሰባት ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን የመሬት ይዞታ በዲጂታል ጂኦ-ሪፈረንስ ክትትል የሚደረግበት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በተለይም በአንድ ጀምበር በሚከናወነው ተከላ ላይ የቴክኖሎጂው አጠቃቀም ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ይደረጋል ብለዋል፡፡ መርሃ ግብሩ በርካታ ትልልቅ ግቦችን ያነገበ ሲሆን፤ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል፣ የምግብ ዋስትና፤ ኢኮኖሚና ቀጣናዊ ትስስርን ማጠናከር ዋነኞቹ ናቸው ብለዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ብቻ ሳይሆን የሥራ ዕድል ፈጠራን፣ የተፋሰስ ልማትን እና የአፈርና ውሃ ጥበቃን ያካተተ ሁለንተናዊ የልማት ስትራቴጂ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስኬት በምሳሌነት የሚወሰድ ነው
Mar 14, 2026 147
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስኬት በምሳሌነት የሚወሰድ የልማት አጀንዳ መሆኑን በኢትዮጵያ የሕንድ አምባሳደር አኒል ኩመር ራይ ገለጹ። አምባሳደር አኒል ኩመር ራይ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በርካታ ችግኞችን በመትከል የካርቦን ልቀትን መቀነስ የሚያስችል ውጤት እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። ከብክለት ነፃ የሆኑ የትራንስፖርት አማራጮችን በማስፋት በኩልም ለአየር ንብረት ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ የኢኮኖሚ መገንባት የሚያስችል ወሳኝ እርምጃ እየወሰደች እንደምተገኝም አንስተዋል። የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስኬት በምሳሌነት የሚወሰድ የልማት አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የኢኮኖሚ ሥርዓት ግንባታም ለሌሎች የአፍሪካ እና የዓለም ሀገራት ተሞክሮ የሚወሰድበት መሆኑን ገልጸዋል። ሕንድም ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሥርዓት ለመገንባት በምታደርገው ጥረት ትብብሯን አጠናክራ እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል። በቅርቡ ለአንድ ጊዜ አገልግሎት የሚሰጡ የፕላስቲክ መያዣዎች ላይ የእግድ ውሳኔ መተላለፉ ለአካባቢ ደኅንነትና ሥነ-ምኅዳር ጥበቃ ጉልህ ፋይዳ ያለው ወሳኝ እርምጃ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይም ሕንድ በአካባቢ ጥበቃና አረንጓዴ ኢኮኖሚ ሥርዓት ያላትን ልምድና ተሞክሮ በማጋራት ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ሁለንተናዊ ትብብር አጠናክራ እንደምትቀጥል ገልጸዋል።
አዋጁ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግብ ለማድረስ ያግዛል
Mar 13, 2026 301
አሶሳ፤ መጋቢት 4/2018(ኢዜአ)፦የተሻሻለው የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ አዋጅ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግብ ለማድረስ እንደሚያግዝ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አካባቢና ደን ጥበቃ እና አየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን አስታወቀ። በክልሉ ህብረተሰቡ በፕላስቲክ ከረጢት ምትክ አማራጭ ምርቶችን በስፋት እንዲጠቀም እየተደረገ መሆኑም ተመላክቷል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሉቅማን አብዱልቃድር እንዳስታወቁት፤ የተሻሻለውን የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ አዋጅ በክልሉ ተግባራዊ ለማድረግ በተለያዩ መድረኮች ህብረተሰቡ ግንዛቤ እንዲኖረው ተደርጓል። በዚህም በፕላስቲክ ምርት ንግድ ላይ የተሰማሩ ግለሰቦች አማራጭ ምርቶችን ማምረት እንዲጀምሩ በተግባር የታገዘ የሙያ ስልጠና እንዲያገኙ መደረጉን ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። በአሁኑ ሰዓት የተወሰኑ ግለሰቦች ተኪ ምርቶችን ማዘጋጀት መጀመራቸውን ጠቁመው፥ በዘርፉ ላይ ለሚሰማሩ አካላት አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግ ተናግረዋል። የፕላስቲክ ከረጢቶች ለአካባቢ ብክለት መንስኤ መሆናቸውን የገለፁት አቶ ሉቅማን አዋጁ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግብ ለማድረስ ያግዛል ብለዋል። አዋጁን ተከትሎ የፕላስቲክ ከረጢቶችን የሚተኩ ምርቶች ላይ የተሰማራችው ወጣት ጅራቱ ሰንበቶ በበኩሏ፤ አዋጁን ተግባራዊ ለማድረግ የህብረተሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ ይገባል ብላለች። በቅርቡ ወደ ስራ መግባቷን ገልጻ አዲስ አበባ በመሄድ ሙያዊ ስልጠና መውሰዷን ተናግራለች። በአሁኑ ሰዓት ሌሎች በዘርፉ የሚሰማሩ የስራ ዕድል ተጠቃሚዎችን ለማሰልጠን ፍላጎት እንዳላት ገልጻ ጎን ለጎንም ለንግድ ተቋማት የወረቀት ከረጢቶችን በማዘጋጀት የማስተዋወቅ ስራ እያከናወነች መሆኑን ተናግራለች። አዋጁን ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ በማድረግ የፕላስቲክ ከረጢቶች የሚያደርሱትን የአካባቢ ብክለትና በህብረተሰቡ ላይ የሚያስከትሉትን የጤና ጠንቅ መከላከል እንደሚገባም ነው የገለጸችው።
በበልግ ዝናብ ተጠቃሚና ሰብል አብቃይ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚኖረው የዝናብ ሁኔታ ለግብርና ስራ አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል
Mar 12, 2026 191
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 3/2018(ኢዜአ)፦ በቀጣዮቹ አስር ቀናት በበልግ ዝናብ ተጠቃሚና ሰብል አብቃይ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚኖረው የዝናብ ሁኔታ ለግብርና ስራ አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለፀ። ኢንስቲትዩቱ ከመጋቢት 2 እስከ መጋቢት 11 ቀን 2018 ዓ.ም የሚኖረውን የአየር ሁኔታ አዝማሚ አስመልክቶ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፤ በቀጣዮቹ አስር ቀናት ለዝናብ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥሩ የሚቲዎሮሎጂ ገፅታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን የልማት እቅዷ አካል በማድረግ በአካባቢ ጥበቃ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች ትገኛለች በልግ ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት በደቡብ እና በደቡብ ምስራቅ፣ የስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎች፣ የመካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንዲሁም በደቡብ ምዕራብ ላይ የተሻለ ገፅታ እንደሚኖራቸው ይጠበቃል። በዚህም በደቡብ፣ መካከለኛው፣ ምስራቅና እና ሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ይጠበቃል። እነዚህ አካባቢዎች በጥቂት ስፍራዎቻቸው ላይ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ። በዚህም መሰረት ወላይታ፣ ጎፋ፣ ጌዴዮ፣ ጋሞ፣ ባስኬቶ፣ አሪ፣ ኮንሶ፣ ቡርጂ፣ አሌ፣ ጋርዱላ፣ ኮሬ እና ደቡብ ኦሞ ዞኖች እንዲሁም ሁሉም የሲዳማ ክልል ዞኖች ከመካከለኛ እስከ ከባድ የዝናብ መጠን ያገኛሉ ብሏል ኢንስቲትዩቱ። ይህ የዝናብ መጠን በቂ የአፈር እርጥበት እንዲኖር፣ የሰብሎች የውሃ ፍላጎት መሟላት፣ ለቋሚ ተክሎች እድገትና የግጦሽ ሳርና የመጠጥ ውሃ አቅርቦት መሻሻል እንዲኖር በማድረግ ለግብርና ሥራ አዎንታዊ ሚና እንዳለው ጠቅሷል። የአፈር መሸርሸር፣ በሰብል ማሳ ላይ ውሃ መተኛት፣ የሰብል በሽታና ተባይ እንዲሁም የአረም መከሰት ሊያስከትል እንደሚችልም አስጠንቅቋል። ስለሆነም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን መስራት፣ የሰብል በሽታንና አረም እንዳይስፋፋ መከላከል፣ የሰብል ማሳዎችን በቅርበት መከታተልና የአየር ጠባይ ትንበያና ምክረ ሃሳቦችን ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል። በመሆኑም የአየር ሁኔታው አስተዋፅኦ በላቀ ሁኔታ ለመጠቀምና ሊከሰት የሚችለውን አሉታዊ ተጽዕኖ ለመቀነስ የሚቲዎሮሎጂ ምክረ ሀሳቦችን ከወዲሁ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አስረድቷል። በሌላ በኩል በጋምቤላ፣ በአፋር፣ በሶማሌ፣ በቤንሻንጉል-ጉሙዝና በምዕራብ አማራ አካባቢዎች ቀን ላይ ከፍተኛ የሙቀት መጠን እንዲሁም ሌሊት ላይ ወበቅ እንደሚጠበቅ ገልጿል።
በጉጂ ዞን ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን በዘላቂነት ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Mar 11, 2026 162
ነጌሌ ቦረና ፤ መጋቢት 2/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በዘንድሮው ዓመት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን በዘላቂነት ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በኦሮሚያ ክልል የተሻሻሉና የአካባቢን ስነ-ምህዳር ታሳቢ ያደረጉ የቡና ችግኞች ይተከላሉ በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ወንዶ ሸርቦቴ ለኢዜአ እንዳሉት፤በዘንድሮ የክረምት ወቅት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው። የችግኝ ዝግጅቱ በዞኑ ባሉ ከ170 በላይ ችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እየተካሔደ ሲሆን እስካሁን ባለው ሒደት 89 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞችን ለማዘጋጀት መቻሉን አስታውቀዋል። ይህም በየዓመቱ የሚከሰተውን ድርቅና የአካባቢ መራቆት ችግርን በዘላቂነት ለመቋቋም እንደሚያስችል ታምኖበታል ነው ያሉት። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካል የሆነው የችግኝ ዝግጅቱ የጉጂ ዞንን ደጋ፣ ወይና ደጋና ቆላማ የአየር ንብረት ታሳቢ ያደረገ መሆኑን አውስተዋል። ለተከላ ከተዘጋጁት የችግኝ ዝርያዎች ውስጥ ጽድ፣ ግራቪሊያ፣ ወይራ፣ ዋንዛ፣ ዝግባና ሌሎችም እንደሚገኙበት ነው ያመለከቱት። እንዲሁም ለከተማ ውበት፣ ለእንስሳት መኖ፣ ለምግብነት የሚውሉና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው እንደ አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ሙዝና ግሽጣ ያሉ ፍራፍሬዎችን ያካተተ የችግኝ ዝግጅት መደረጉን አስረድተዋል። ችግኞቹን ለማልማትና ለውጤት ለማብቃት ከሰውና ከእንስሳት የተከለለ ከ21 ሺህ 340 ሄክታር በላይ መሬት መዘጋጀቱን አስረድተዋል። በመጪው ክረምት በሚካሄደው የችግኝ ተከላ ስራ ከ205 ሺህ በላይ ህዝብ ለማሳተፍ የቅስቀሳና የግንዛቤ ማሳደግ ስራ እየተካሄደ እንደሚገኝም አመላክተዋል። በዞኑ ባለፈው ዓመት ከተተከሉት ችግኞች በህዝብ እንክብካቤና ጥበቃ 83 በመቶው መጽደቁን በመስክ ምልከታና ክትትል ለማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል።
በክልሉ በበልግ ወቅት እየጣለ ባለው ዝናብ ጎርፍን ጨምሮ የመሬት መንሸራተት አደጋ እያጋጠመ በመሆኑ አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግ ኮሚሽኑ አሳሰበ
Mar 10, 2026 195
አርባምንጭ ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የበልግ ወቅትን ተከትሎ እየጣለ ባለው ዝናብ ጎርፍን ጨምሮ የመሬት መንሸራተት አደጋ እያጋጠመ በመሆኑ ህብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራርና የምግብ ዋስትና ኮሚሽን አሳሰበ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራርና የምግብ ዋስትና ኮሚሽን ኮሚሽነር ወገኔ ብዙነህ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የበልግ ወቅትን ተከትሎ እየጣለ ያለው ዝናብ በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ የጎርፍና የመሬት መንሸራተት አደጋ እያስከተለ ነው። በክልሉ በጋሞ፣ በወላይታ፣ በደቡብ ኦሞ፣ በኮንሶ፣ በጌዲኦ እና በጎፋ ዞኖች በሚገኙ ተራራማ አካባቢዎች ያልተጠበቀ የመሬት መንሸራተት እንዲሁም በአንዳንድ ቆላማ አካባቢዎች ደግሞ የጎርፍ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል አመላክተዋል። ስለሆነም ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ የክልሉ ነዋሪዎች አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባ አሳስበዋል። ህብረተሰቡ በየአካባቢው አጠራጣሪ የሆኑ የመሬት መሰንጠቆች፣ የውሃ ምንጮችና ሌሎች ለውጦች ሲከሰቱ በፍጥነት ለሚመለከተው ክፍል መረጃ በመስጠት ብሎም ስጋት ወደሌለባቸው አካባቢዎች በመሄድ ራሱን ከአደጋው እንዲጠብቅ አስገንዝበዋል። ኮሚሽነር ወገኔ አክለውም በክልሉ የተፈጥሮ አደጋዎችን በዘላቂነት ለመከላከልም በአረንጓዴ አሻራና የተፋሰስ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አስረድተዋል። ከዚህ ቀደም በክልሉ በተለያዩ ዞኖች በተፈጥሮ አደጋ ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን ስጋት ወደሌለባቸው አካባቢዎች በማስፈር መልሶ የማቋቋም ስራ ሲከናወን መቆየቱን አስታውሰዋል። ችግሩን በሳይንሳዊ መንገድ በዘላቂነት ለመከላከል በጥናት ላይ የተመሰረተ ስራ እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል። የጋሞ ዞን አደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መስፍና ማኑቆ በበኩላቸው፤ ትናንት ምሽት በጣለው ከፍተኛ ዝናብ በዞኑ ቦንኬ እና ጋጮ ባባ ወረዳዎች በመሬት መንሸራተት አደጋ የሰው ህይወት ማለፉን ገልጸዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ እና ዙሪያ ወረዳ የኩልፎ እና የሴጎ ወንዞች ሙላት ባስከተሉት የጎርፍ አደጋ በተለያዩ ተቋማትና መሠረተ ልማት ላይ ጉዳት ማድረሱን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የአደጋው መጠን እየተጣራ መሆኑን ጠቁመው ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን መልሶ ለማቋቋም ከነዋሪዎች፣ ከግብረ-ሰናይ ድርጅቶችና ከባለሀብቶች ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን የልማት እቅዷ አካል በማድረግ በአካባቢ ጥበቃ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች ትገኛለች
Mar 10, 2026 200
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን በሀገራዊ የልማት እቅዷ ውስጥ በማካተት በአካባቢ ጥበቃ ረገድ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች መሆኗን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ገለፁ። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ከህንድ የሳይንስና አካባቢ ማዕከል ጋር በመተባበር ያዘጋጁት በሰርኩላር ኢኮኖሚ ላይ የሚያተኩረው 8ኛው የከተሞች ፎረም ከመጋቢት 1 እስከ 3 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) በፎረሙ መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት፣ የሰርኩላር ኢኮኖሚ መርህ የአየር ንብረት የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ እና የ10 ዓመቱ የልማት እቅድ አካል ነው። ስትራቴጂው የኢኮኖሚ እድገትን ከአካባቢ ጥበቃ ጋር ማስተሳሰር፣ ዘላቂ የቆሻሻ አያያዝን እና መልሶ ጥቅም ላይ ማዋልን ማጠናከር እንዲሁም በአረንጓዴ ስራ ፈጠራ በተለይም ወጣቶችንና ሴቶችን ተጠቃሚ ማድረግ ላይ ያለመ ነው ብለዋል። በተጨማሪም በግብርና፣ በምግብ ስርዓት እና በግንባታ ዘርፎች ላይ ያተኮረ ብሄራዊ የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ-ካርታ ወደ ትግበራ መሸጋገሩን ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለምርምር፣ ለቴክኖሎጂ ሽግግር እና ለግል ዘርፉ ተሳትፎ ማዕከል የሚሆን "የሰርኩላር ኢኮኖሚ የልህቀት ማዕከል" በአዲስ አበባ የማቋቋም ሂደት መጀመሯን ገልጸዋል፡፡ ማዕከሉ የሀብት ምርታማነትን በማሳደግ እና በመላው አፍሪካ የአጋርነት ትስስርን በመፍጠር ረገድ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረውም ጠቅሰዋል፡፡ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፋንታ ደጀን በበኩላቸው በኢትዮጵያ የከተማ ልማት ስራዎች ከአካባቢ ጥበቃ ጋር ተሰናስለው እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። የሰርኩላር ኢኮኖሚ ከተሞች ሀብትን በብክነት ፈንታ ወደ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እንዲቀይሩ የሚያስችል ማዕቀፍ መሆኑን አስገንዝበዋል። በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩመር ራይ በአፍሪካ እየታየ ላለው ፈጣን የከተሞች መስፋፋት ተስማሚ የአካባቢ ጥበቃ መፍትሄዎች እንደሚያስፈልጉ ገልጸዋል። በዚህም ኢትዮጵያ በኮሪደር ልማት እያከናወነች ያለው ተግባር ለሌሎች ሀገራት ትልቅ ትምህርት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መሪነት የተከናወኑ የልማት ስራዎች ከተማን እንዴት መለወጥ እንደሚቻል በተግባር ማሳየት መቻሉን ጠቅሰው አዲስ አበባ አሁን ላይ ሰፋፊ መንገዶች፣ የብስክሌት መጓዣያዎች እና አረንጓዴ ስፍራዎች ያሏት ዘመናዊ ከተማ መሆኗን ጠቁመዋል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል
Mar 9, 2026 244
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30 /2018(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር ማስቻላቸውን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ። የኢትዮጵያ የአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ተምሳሌታዊ ተግባር ነው የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ ፈጠራና የሕግ ተከባሪነት ስኬታማ ስራ ተሰርቷል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶችም የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ለፅዱ ኢትዮጵያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ገልጸዋል። የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የፕላስቲክ፣ የአፈር፣ የውሃ፣ የአየርና የድምፅ ብክለትን በመከላከል የአካባቢና ማህበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ ላይ ትኩረት ማድረጉን ተናግረዋል። በንቅናቄው መሠረት በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ15 ሚሊየን በላይ ከሚሆን ህዝብ ጋር የገፅ ለገፅ መድረክ በመፍጠር የአካባቢ ጥበቃና ፅዱ አካባቢ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት መሰጠቱን አንስተዋል። በመገናኛ ብዙሃንም ከ50 ሚሊየን በላይ ህዝብ ተደራሽ በማድረግ ህብረተሰቡ በአካባቢ ላይ የሚደርስ ብክለትን መቀነስ የሚያስችል የዕውቀት፤ የግንዛቤና የሕግ ማስከበር ሥራ መሰራቱን አስረድተዋል። በዚህም በሁለት ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የዜጎችን የአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ በማሳደግ ፅዱና የበለፀገች ኢትዮጵያን ለትውልድ ማስተላለፍ የሚያስችል መሰረት መጣሉን ጠቅሰዋል። በቀጣይም 3ኛ ዙር የፅዱ ኢትዮጵያን ባህል እናድርግ ሀገር አቀፍ ንቅናቄ ለማስጀመር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። በ3ኛው ዙር ሀገር አቀፍ ንቅናቄም የለውጡን ዓመታትን የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች በማጽናት ባህል ይሰራል ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተተገበሩ የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የገጠርና ከተማ ኮሪደር ልማት ስኬቶች የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ለፅዱ ኢትዮጵያ ግንባታ ወሳኝ ሚና እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል። የኮሪደር ልማት ስራ የፍሳሽ አወጋገድና የቆሻሻ አያያዝን በማዘመን ዜጎችን ፅዱ የመኖሪያ ምኅዳር በማጎናጸፍ የወንዞችን ጤናማነት የሚያስጠብቅ ተምሳሌታዊ የልማት ስኬት መሆኑንም ተናግረዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃና የእርከን ሥራ የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በማስጠበቅ ገንቢ ሚና እየተወጣ እንደሚገኝ አንስተዋል። በሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታም ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚሰሩ የግሉን ዘርፍ ማበረታታት የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑንም አመላክተዋል።