አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በመዲናዋ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ለፍራፍሬ ችግኞች ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል
Jun 18, 2026 24
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 11/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ለዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የፍራፍሬ ተክሎችን በስፋት ያካተቱ አምስት ሚሊየን ችግኞች መዘጋጀታቸውን የከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ኃላፊ ግርማ ሰይፉ ገለጹ። ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሐሳብ አመንጪነት ከ2011 ዓ.ም. ጀምሮ በተከታታይ ባከናወነችው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር እስካሁን 48 ቢሊየን ችግኞችን መትከል ችላለች። የአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ብልጽግና ለማረጋገጥ ከሀገራዊ ሕልሟ ጋር የተቆራኘ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበበት ይገኛል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር በቢሾፍቱ በይፋ ባስጀመሩበት ወቅት እንደገለጹት፣ በዘንድሮው ዓመት ብቻ ስምንት ቢሊየን ችግኞችን ለመትከል ግብ ተቀምጧል። አባቶቻችን በአድዋ ላይ ታሪካዊ ገድል ፈጽመው ሀገር እንዳስረከቡን ሁሉ፣ የአሁኑ ትውልድም በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ሌላኛውን የአረንጓዴ አርበኝነት ገድል እየደገመ ይገኛል። ይህ ታላቅ ሀገራዊ ንቅናቄ የሚፈጥረው የአየር ንብረት ለውጥ የመቋቋም አቅምና የምግብ ሉዓላዊነት ስኬት፣ ለቀጣዩ ትውልድ ሉዓላዊነቷ የተረጋገጠና የበለጸገች ሀገር ለማስረከብ ለተጀመረው ጉዞ እንደ ትልቅ ምሰሶ የሚቆጠር ነው። የአዲስ አበባ ከተማ የውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ኃላፊ ግርማ ሰይፉ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በመዲናዋ ዘንድሮ ለሚከናወነው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የዝግጅት ሥራ ተጠናቋል። በአሁኑ ወቅትም የችግኝ ማፍላትና የቦታ መረጣ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰው የጉድጓድ ቁፋሮ ሥራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በከተማዋ ከዚህ ቀደም የተተከሉ ችግኞች የፅድቀት ምጣኔ በጥሩ ሁኔታ ላይ መሆኑን ጠቁመው፣ በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር የፍራፍሬ ችግኞችን በስፋት ያካተቱ አምስት ሚሊየን ችግኞች እንደሚተከሉ አስታውቀዋል። በመሆኑም ወጣቶች እና ሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች በዘንድሮው የችግኝ ተከላና እንክብካቤ ሥራ ላይ በንቃት እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል። በሱሱኒ ችግኝ ጣቢያ የዘር ብዜትና የችግኝ እንክብካቤ ባለሙያ ተሾመ ፉፋ እንደገለጹት በጣቢያው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብርን ስኬታማ ለማድረግ ከፍተኛ ዝግጅት መደረጉን አንስተዋል፡፡ ይህንንም ተከትሎ በጣቢያው አንድ ነጥብ አምስት ሚሊየን ችግኞች ለተከላ ዝግጁ የተደረጉ ሲሆን በርካታ የተዳቀሉ የፍራፍሬ ዘር ችግኞች መዘጋጀታቸውን አረጋግጠዋል። ችግኞቹ ለታለመላቸው ዓላማ እንዲውሉ ተከታታይ ክትትልና እንክብካቤ እንደሚያስፈልጋቸው የተናገሩት ደግሞ ሌላኛዋ ባለሙያ የሆኑት ፅጌ ነጋ ናቸው። አረንጓዴ ዐሻራን ከግብ ለማድረስ ችግኝን መትከል ብቻ ሳይሆን ተገቢውን እንክብካቤ ማድረግም ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል።
በክልሉ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የደን ሃብት ሽፋንን ከማሳደግ ባለፈ የከርሰና ገጸ ምድር ውሃ መጠን እንዲጨምር አስችሏል
Jun 18, 2026 89
ባህር ዳር፤ ሰኔ 11/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የደን ሃብት ሽፋንን ከማሳደግ ባለፈ የከርሰና ገጸ ምድር ውሃ መጠን በመጨመር የመስኖ ልማትን ለማሳደግ ማገዙን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለፀ። የቢሮው ምክትል ሃላፊ ወይዘሮ መሰሉ ብርሃኑ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በክልሉ ህብረተሰቡን በማሳተፍ የተከናወኑ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሀ ግብር ትግበራ የደን ሃብት ሽፋኑን ከማሻሻል በተጨባጭ የአፈር መከላትን መከላከል አስችሏል። እንዲሁም የክልሉን የደን ሃብት ሽፋን ከ14 ነጥብ 6 በመቶ ወደ 18 ነጥብ 9 በመቶ ማሳደግና የከርሰ ምድርና ገፀ ምድር ውሃ ሀብትን በማሳደግ የመስኖ ልማትን ለማሳደግ ማገዙን ጠቁመዋል። ዘንድሮም ተግባሩን በማስቀጠል የክረምት ወቅት የፍራፍሬ፣ የውበት፣ የደንና ሌሎች ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል። ችግኝ ተከላውን በ261 ሺህ 460 ሄክታር መሬት ላይ ለማከናወን የጉድጓድ ቁፋሮ ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። በዚህ ዓመት ለሚከናወነው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ውጤታማነትም በየደረጃው የሚገኘው አመራር፣ ወጣቶችና ሴቶች ብሎም መላው ህብረተሰብ በባለቤትነት እንዲሳተፍም ጠይቀዋል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ግብርና መምሪያ ሃላፊ የሰውዘር ደመላሽ በበኩላቸው በከተማው ለሚከናወነው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት መጠናቀቁን ተናግረዋል። ችግኞቹን ለመትከል የቦታ ልየታን ጨምሮ የመትከያ ጉድጓድ ቁፋሮ መከናወኑን ገልፀው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ላላቸው፣ ለደን እና ለውበት የሚሆኑ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር በችግኝ ማፍላት ለተሰማሩ ወጣቶች መልካም አጋጣሚ በመፍጠር በኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረጉን የገለፀው ደግሞ በባህር ዳር ከተማ በችግኝ ማፍላት ስራ ላይ የተማራው ወጣት ንጉስ ቻሌ ነው። ሦስት ሆነው በመደራጀት ችግኞችን አፍልተው ለገበያ በማቅረብ ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሶ፤ በዚህ ዓመት ለሚከናወነው ችግኝ ተከላም 70 ሺህ ችግኞችን ማዘጋጀታቸውን ገልጿል።
በጋሞ ዞን ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል
Jun 17, 2026 548
አርባምንጭ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በጋሞ ዞን በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የተፈጥሮ ሀብት ልማት ቡድን መሪ አቶ ስንታየሁ መኮንን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢንሼቲቭ የተጀመረው የአረንጓዴ አሻራ ልማት በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ ነው። በዞኑ ለዘንድሮው የክረምት ወራት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ለፍራፍሬ፣ ለደን፣ ለጥምር ደን፣ ለእንስሳት መኖ የሚሆኑና ሌሎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል ብለዋል፡፡ በዞኑ በማህበራት፣ በቡድን፣ በፕሮጀክት፣ በመንግስትና በግለሰብ ደረጃ የሚለሙ 397 ችግኝ ጣቢያዎች መኖራቸውን ጠቅሰው አስፈላጊው ችግኝ በበቂ ሁኔታ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። በዚህም ከ24 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ ተከላው እንደሚከናወን ጠቅሰው ለዚህም አስፈላጊው ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል፡፡ ለክረምቱ መደበኛና ለአንድ ጀምበር መርሃ-ግብሮች ስኬት የጉድጓድ ቁፋሮ ዝግጅት እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። የአርባ ምንጭ ዙሪያ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ መርደኪዮስ ኬርባ በበኩላቸው የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር የሰው ልጅ ከእጽዋት ጋር ያለውን መስተጋብር በተጨባጭ ያሳደገ ነው ብለዋል። በተጨማሪም የአየር ሚዛንን በማስተካከልና የአካባቢን ስነ ምህዳር በመጠበቅ ምርትና ምርታማነትን ለማረጋገጥ ጉልህ ሚና እያበረከተ መሆኑን ገልጸው በዘንድሮው ተከላም ህዝቡን በነቂስ ለማሳተፍ በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ ለዚህም የችግኝ ዝግጅትና የጉድጓድ ቁፋሮ ስራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ ልማት የሚያስገኘውን ጥቅም ህብረተሰቡ በአግባቡ እየተረዳ መምጣቱን የገለጹት ደግሞ በምዕራብ አባያ ወረዳ የኡጋዮ ቀበሌ አርሶ አደር ጀማል አንጃ ናቸው። በተለይ እስካሁን በተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ስራዎች የተጎዱ መሬቶች እያገገሙ፣ የደረቁ ምንጮች እየፈለቁና የሙቀት መጠን ሚዛኑ እየተስተካከለ መምጣቱን በተጨባጭ እያየን ነው ብለዋል። በመርሃ ግብሩ የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ ለምግብነትና ለኢኮኖሚ ምንጭነት እያገለገሉ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። በየጊዜው በሚካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር ሲሳተፉ መቆየታቸውን ጠቅሰው በዘንድሮው ዘመቻ ሙሉ ቤተሰባቸውን በማስተባበር ለችግኝ ተከላው መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል፡፡
ኢትዮጵያ በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ላይ እየተጫወተች ያለው የመሪነት ሚና በአስተማማኝ መሠረት ላይ እየተገነባ ነው
Jun 17, 2026 428
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ላይ እየተጫወተች ያለው የመሪነት ሚና በአስተማማኝ መሠረት ላይ እየተገነባ መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን ገለጹ። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ከኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ጋር በመተባበር በቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ያስገነባውን ግዙፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሙያ ጣቢያ አስመርቋል፡፡ የትራንስፓርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን በወቅቱ ባስተላለፉት መልእክት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ መሙያ ጣቢያዎችን በማስፋፋት ላይ ትገኛለች፡፡ በአሁኑ ወቅት በርካታ ፈጣን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ቻርጅ መሙያ ጣቢያዎች በስፋት እየተገነቡ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ይህም አገሪቱ በዘርፉ ላይ እየተጫወተች ያለው የመሪነት ሚና በአስተማማኝ መሠረት ላይ እየተገነባ ለመሆኑ ማሳያ ነው ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ተግባራዊ ምላሽ እየሰጠች መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የዚህ ግዙፍ የቻርጅ መሙያ ጣቢያ እውን እንዲሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት ምስጋናቸውን ያቀረቡ ሲሆን፣ በቀጣይም በዘርፉ ለሚከናወኑ ስራዎች የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል፡፡
የኢትዮጵያ የአረንጓዴ የልማት አቅጣጫ በሁሉም ዘርፍ ዕድገትን የሚያፋጥን ስኬት እያስገኘ ነው
Jun 17, 2026 358
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የአረንጓዴ የልማት አቅጣጫ በሁሉም ዘርፍ ዕድገትን የሚያፋጥን ስኬት እያስገኘ መሆኑን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍስሀ ይታገሱ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ከኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ጋር በመተባበር በቂሊንጦ ልዩ ኢኮኖሚ ዞን ያስገነባውን ግዙፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሙያ ጣቢያ የምርቃት መርሀግብር በመካሄድ ላይ ነው። በመርሀግብሩ የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል። የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሰሃ ይታገሱ (ዶ/ር)፤ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሙያ ጣቢያው ወቅታዊ እና አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ኢትዮጵያ እየተከተለችው ያለው የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ፖሊሲ አንዱ አካል መሆኑን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ የልማት አቅጣጫ በሁሉም ዘርፍ ዕድገትን የሚያፋጥን ስኬት እያስገኘ መሆኑንም አንስተዋል። ከዚህም አንዱ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች መሆናቸውን ተናግረው፤ ወደፊት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ፍላጎት ለማሟላት ቻርጅ የማድረጊያ ጣቢያዎችን ማስፋት እንደሚገባ ጠቁመዋል። በዛሬው እለት ለምረቃ የበቃው የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሙያ ጣቢያ በወሳኝ ወቅት የመጣ እርምጃ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ዋና መሪ ቃል አካባቢን የማይበክል አምራች ኢንዱስትሪ መሆኑንም በመግለጽ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሙያ ጣቢያው ከመሪ ቃሉ ጋር የተጣጣመ መሆኑን አንስተዋል። ተቋማቱ ጥብቅ ቁርኝነት ያላቸው መሆኑን ገልጸው፤ በቀጣይም በትብብር እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል።
አገልግሎቱ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ለማሳለጥ የበኩሉን ሚና እየተወጣ ነው
Jun 17, 2026 327
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት በአገሪቱ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታን ለማሳለጥ የበኩሉን ሚና እየተወጣ መሆኑን የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው ገለጹ። የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ከኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ጋር በመተባበር ያስገነባውን ግዙፍ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሙያ ጣቢያ ሥራ አስጀምሯል፡፡ በዚሁ መርሀግብር ላይ የትራንስፖርት እና ሎጅስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በርኦ ሀሰን፣ የኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሰሃ ይታገሱ (ዶ/ር)ን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጂነር ጌቱ ገረመው በዚሁ ወቀት፤ ተቋሙ እንደ አገር የተያዘውን የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ መሠረት በማድረግ አስተማማኝ ኃይል እያቀረበ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ዛሬ ለምረቃ የበቃው ፈጣን የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሙያ ጣቢያ ለአገልግሎቱ አራተኛው ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም ይህንን መሠረተ-ልማት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች አጠናክሮ ለማስፋፋት መታቀዱን ተናግረዋል። በተለይም ከፍተኛ ንግድ መስመር በሆነው በኢትዮ-ጅቡቲ ኮሪደር ላይ 16 የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ መሙያ ጣቢያዎችን ለመገንባት በአሁኑ ወቅት የዲዛይን ሥራ እየተሠራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው ለአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ለአካባቢው ስነምህዳር የሚስማሙ ችግኞችን አዘጋጅቷል
Jun 17, 2026 227
አሶሳ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦አሶሳ ዩኒቨርሲቲ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ለአካባቢው ስነምህዳር ተስማሚ የሆኑ ችግኞችን ማዘጋጀቱን አስታወቀ። በዩኒቨርሲቲው በግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ኮሌጅ የደን አያያዝና እንክብካቤ መምህር እና ተመራማሪ አህመድ አሊ እንደገለጹት፣ ዩኒቨርሲቲው ካለፈው ዓመት ጀምሮ ለአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የበኩሉን ድርሻ እየተወጣ ነው። በየዓመቱ የተለያየ ኢኮኖሚያዊ ጠቃሜታ ያላቸውን የደን እና የፍራፍሬ ችግኞች በማዘጋጀት በራሱ ከሚተክለው ባለፈ ለአካባቢው ማህበረሰብ በማድረስ ለመርሀግብሩ ስኬታማነት የበኩሉን መወጣቱን ገልጸዋል። ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብርም በዩኒቨርሲቲው በሚገኝ የችግኝ ማፍያ ጣቢያ ከ18 በላይ የችግኝ አይነቶችን በማፍላት ለተከላ ዝግጁ ማድረጉን ገልጸዋል። ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ካላቸውና ከተሻሻሉ ችግኞች መካከል ቡና፣ አቮካዶ፣ ብርቱካን፣ ማንጎ እና ሌሎችም እንደሚገኙበት ተናግረዋል። በተለይም ዩኒቨርሲቲው ከጅማ ግብርና ምርምር ያስመጣቸው የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎች ለአካባቢው ስነምህዳር ተስማሚ መሆናቸው በመረጋገጡ በቀጣይ ለአካባቢው ማህበረሰብ ተደራሽ ለማድረግ ታቅዷል ብለዋል። በዩኒቨርሲቲው የችግኝ ማፍያ ጣቢያ ከ63 ሺህ በላይ ችግኞች መኖራቸውን ገልፀው፣ ችግኝ ጣቢያው በተግባር የታገዘ ትምህርት ለመስጠት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም አስታውቀዋል። ዩኒቨርሲቲው ባለፈው ዓመት ኡራ እና አቡራሞ ወረዳዎች ላይ የተከላቸው የደን ችግኞች የጽድቀት መጠን በጥሩ ደረጃ ላይ መሆኑንም አስታውሰዋል። እንደ መምህርና ተመራማሪ አህመድ ገለጻ በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የተፈጥሮ ሀብት ልማት እና ጥበቃ ሥራዎች የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመጠበቅ ባለፈ የደን ሀብት እንዲጨምር አድርገዋል። ለዜጎች የሥራ ዕድል በመፍጠር የኢኮኖሚ ምንጭ በመሆን ጉልህ ሚና እየተጫወቱ መሆኑንም መምህሩ ጠቁመዋል።
የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ የኢትዮጵያን ዘላቂ ልማት ለማረጋገጥ የጎላ ሚና አለው
Jun 17, 2026 149
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ሀገራዊ ሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ የኢትዮጵያን ዘላቂ ልማት ለማረጋገጥ የጎላ ሚና እንዳለው በኢትዮጵያ የፊንላንድ ኤምባሲ የትብብር ኃላፊ ቶሚ ሳርኪዮጃ ገለፁ። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ከአፍሪካ ልማት ባንክ ጋር በመተባበር የሀገራዊ ሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ ይፋ አድርጓል። ኢትዮጵያ በሀገር አቀፍ ደረጃ የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስ እና አረንጓዴ ኢኮኖሚን ለመገንባት"የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታ" (Circular Economy Roadmap) በማዘጋጀት ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ እንዲውል የማበረታታት ስራዎችን እየሰራች ትገኛለች። እንደ አዲስ አበባ ይህንን ፍኖተ ካርታ ወደ መሬት በማውረድ ከከተማዋ እድገት ጋር ተያይዞ የሚመጣውን የቆሻሻ አያያዝ ስጋት ወደ መልካም አጋጣሚ ለመቀየር በርካታ ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች እየተደረጉ ይገኛሉ። ይህን በተመለከተ በኢትዮጵያ የፊንላንድ ኤምባሲ የትብብር ኃላፊ ቶሚ ሳርኪዮጃ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ ኢትዮጵያ በሰርኩላር ኢኮኖሚ ፖሊሲዎቿና መጠነ-ሰፊ በሆኑ የአካባቢ ጥበቃ መርሃ-ግብሮቿ አማካኝነት ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ አበረታች እርምጃዎችን እየወሰደች መሆኑን ተናግረዋል። ፊንላንድ በዚህ ዘርፍ ያላትን ሰፊ ልምድ መሠረት በማድረግ ከአካባቢ ጥበቃ ባለፈ ለኢኮኖሚ ዕድገት ከፍተኛ ዕድሎችን በያዘው የቆሻሻ አወጋገድ እና መልሶ ጥቅም ላይ ማዋል (ሰርኩላር ኢኮኖሚ) ዘርፍ ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር እየሠራች መሆኑን ኃላፊው ጠቁመዋል። ዘርፉ ለአካባቢ ጥበቃም ሆነ ለንግድ ተቋማት የጋራ ተጠቃሚነትን የሚፈጥር በመሆኑ እጅግ አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ ብሔራዊ ሰርኩላር ኢኮኖሚ እና መልሶ ጥቅም ላይ ማዋል ፍኖተ ካርታ በማዘጋጀትና ዘላቂ የንግድ አሠራሮችን የሚያበረታታ የፖሊሲ ምኅዳር መፍጠሯ አበረታች ነው ብለዋል። ይህ የሰርኩላር ኢኮኖሚ አጀንዳ ከሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ-ግብርና ከአረንጓዴ አሻራ ተነሳሽነት ጋር ፍጹም የሚጣጣም መሆኑን ተናግረዋል። ለአካባቢ ጥበቃና ለዘላቂ ዕድገት አስተዋጽኦ የሚያደርጉ በመሆናቸው እርስ በርሳቸው የሚደጋገፉ መሆናቸውንም አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በአካባቢ ጥበቃ ረገድ እያገኘች ስላለው ዓለም አቀፍ ዕውቅና ሀገሪቱ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤን (COP32) ለማስተናገድ መመረጧን እንደ ትልቅ ማሳያ ጠቅሰዋል።
በዞኑ በአሳታፊ የደን ልማት የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመጠበቅ ባሻገር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል
Jun 17, 2026 100
ደብረ ማርቆስ ፤ ሰኔ 10/2018 (ኢዜአ)፦ በምስራቅ ጎጃም ዞን በአሳታፊ የደን ልማት የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመጠበቅ ባሻገር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉን የዞኑ አካባቢ ጥበቃ ተጠሪ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የተጠሪ ጽህፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ መለሰ መንግስት ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ በአሳታፊ የደን ልማት የአካባቢን ስነ ምህዳር ከመጠበቅ ባሻገር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል። በዞኑ በመንግስት፣ በግል፣ በማህበራትና በማህበረሰብ ይዞታነት የተመዘገቡ ከ319 ሺህ ሄክታር በላይ ደኖችን በመጠበቅ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታቸውን ለማጉላት እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም ደኖችን ከመንከባከብ ባለፈ ነባር ደኖችን ለኢንዱስትሪ ግብዓት በማዋል የተቆረጡትን በአዲስ የመተካት ስራ እየተከናወነ ነው ብለዋል። በዚህም በበጀት ዓመቱ 77 ሺህ 256 ሜትር ኪዩብ የጽድ፣ የባህር ዛፍና ሌሎች የደን ውጤቶችን እንዲሁም 275 ኩንታል እጣን ለሽያጭ በማቅረብ ከ10 ነጥብ 7 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ መገኘቱን ጠቅሰዋል። ለኢኮኖሚያዊ ጥቅም የዋለውን ደን ለመተካት ከ570 ሄክታር በላይ በሆነ መሬት ላይ ከ2 ነጥብ 7 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ለመትከል የጉድጓድ ቁፋሮ ስራ እየተከናወነ መሆኑን አስረድተዋል። በደን ልማት ዘርፉም ለ6 ሺህ 343 የህብረተሰብ ክፍሎች ቋሚና ጊዜያዊ የስራ እድል እንደተፈጠረም ተናግረዋል። በአነደድ ወረዳ የአንበር ዙሪያ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ዋስይሁን ዘሩ፤ በአካባቢያቸው የሚገኘውን የማህበረሰብ ደን በመጠበቅና በመንከባከብ ለምርት ማብቃታቸውን ገልጸዋል። የደረሰውን ምርት ለእንጨትና ለጣውላ ፋብሪካዎች በመሸጥ ከ1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘታቸውን ጠቁመው ለጥቅም የተቆረጠውን ደን መልሰን እየተካን ነው ብለዋል። የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አቶ እውነቱ ይበልጣል በበኩላቸው፤ የደን ልማት አፈር በጎርፍ እንዳይጠረግ ከማድረጉም በላይ የቀጥታ ኢኮኖሚ ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ ቀደምም ለምርት የደረሰውን ደን በመሸጥ ለትምህርት ቤት ግንባታ ድጋፍ ማዋላቸውን ጠቁመው አሁን የተገኘውን ገቢም ለማህበራዊ ልማት ለማዋል እየሰራው ነው ብለዋል።
በአረንጓዴ ዐሻራ ጸንቶና ተግቶ መሥራት ዘመኑ የሚፈልገው ዐርበኝነት
Jun 17, 2026 154
በዮሐንስ ደርበው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሐሳብ በቢሾፍቱ አስጀምረዋል። መርሐ-ግብሩ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ብልጽግና አሠናሥሎ የሚያረጋግጥ ብሔራዊ ኢኒሼቲቭ መሆኑንም በዚሁ ወቅት በአጽንዖት ገልጸዋል። በተጨማሪም የደን፣ የሰብልና ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ወሳኝ የልማት አቅጣጫም ነው። ከ8 ቢሊየን በላይ ችግኞች ለተከላ ዝግጁ በሆኑበት በዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ ወቅት፤ አረንጓዴ ለሆነች ነገ፣ ሁላችንም ተስፋን እንትከል ሲሉም ለሀገሬው ጥሪ አቅርበዋል። አረንጓዴ ዐሻራ - ለዓየር ንብረት ለውጥ ላለመበገር የሚደረግ ትጋት ከአፍሪካ ሰማይ እስከ ዓለም ከፍታ • ከችግኝ ተከላ ያለፈ ድርብርብ ጥቅም ያለው ኢኒሼቲቭ የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ለሀገር በቀል ችግኞች፣ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ላላቸው አትክልትና ፍራፍሬዎች፣ ለውበት የሚሆኑ ዛፎች፣ የተራቆቱ መሬቶችን እንዲያገግሙ ያሚያስችሉ እና የደን ሽፋንን በማሳደግ ለከባቢ አየር መስተካከል ከፍተኛ አስተዋጽዖ እያበረከቱ ያሉ ችግኞች የሚተከሉበት ነው። በዚህ ሁሉ ሂደት የአፈር መሸርሸርና መከላት ቀንሷል፣ የጎርፍ አደጋዎች ቀንሰዋል፣ የብዝኃ ሕይወት መመናመን ቀንሷል፣ የመሬት መራቆት ቀንሷል፣ የውኃ አካላት በደለል መሞላትና መጥፋት ቀንሷል፤ በአንጻሩ ምርትና ምርታማነት ጨምሯል። ነገ ከዚህ የበለጠ ውጤት እንዲገኝ ዛሬ ላይ ኢትዮጵያውያን የሕዝብን ተጠቃሚነት በሚያረጋግጠው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር በነቂስ መሳተፍ ይጠበቅባቸዋል። አረንጓዴ ዐሻራ ከተጀመረ ጀምሮ ላለፉት ዓመታት ከ48 ቢሊየን በላይ ችግኞችን በመትከል ከሀገራዊ ለውጡ በፊት 17 ነጥብ 2 በመቶ የነበረውን የደን ሽፋን አሁን ወደ 23 ነጥብ 6 በመቶ ከፍ ማድረግ ተችሏል። በሕዝቡ ዘንድ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብር ተፈጥሮን የመንከባከብ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፤ የሀገርን የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትና የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ጉዳይ ጭምር ተደርጎ መወሰድ ይኖርበታል። ይህ ዘርፈ-ብዙ ጥቅሙ በተጨባጭ እየተገለጠ ያለው የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ2011 ዓ.ም መጀመሩ ይታወሳል። #ተስፋን_እንትከል #ኢዜአ #አረንጓዴ_ዐሻራ
በባሌ ዞን ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Jun 16, 2026 518
ሮቤ፤ ሰኔ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። የዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ-ግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች በተገኙበት በይፋ ተጀምሯል። ዘንድሮ የተያዘውን የ8 ቢሊዮን ችግኞችን የመትከል ግብ ለማሳካት በሚደረገው ብሔራዊ የንቅናቄ ሥራ ላይ በሁሉም የማኅበረሰብ ክፍሎች የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ለተግባራዊነቱ እንዲረባረቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጥሪ ማቅረባቸውም ይታወሳል። በኦሮሚያ ክልል ባሌ ዞን የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ስኬታማ ለማድረግ ህብረተሰቡን ያሳተፈ ሥራ እየተሠራ ይገኛል። የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ሙአዊያ ፉአድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዞኑ ባለፉት ዓመታት ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ በተከናወነው መርሃ ግብር የተራቆተ መሬትን መልሶ በደን በመሸፈን ረገድ ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል። ይህንን ተግባር ለማስቀጠልም በመጪው ክረምት የሚተከሉ ከ229 ሚሊዮን የሚበልጡ ችግኞችን በመንግስት፣ በማህበራትና በግል የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች የማዘጋጀቱ ሥራ ተጠናክሮ ቀጥሏል። እስካሁን ከ211 ሚሊዮን በላይ ችግኞች የተዘጋጁ ሲሆን፣ 194 ሚሊዮን የሚሆኑ የመትከያ ጉድጓዶች መዘጋጀታቸውንና ቀሪው ሥራ እየተከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። በዞኑ በችግኝ ማፍያ ጣቢያዎቹ በአብዛኛው ሀገር በቀልና ሌሎች የውጭ ዝርያ ችግኞች መዘጋጀታቸውን የገለጹት ደግሞ በጽህፈት ቤቱ የተፋሰስና የደን ልማት ቡድን መሪ አቶ ተስፋዬ ኦሊቃ ናቸው። አካባቢው በዓመት ሁለት ጊዜ የበልግና የክረምት ዝናብ የሚያገኝ በመሆኑ ተከላውም ይህንን ስነ-ምህዳር ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ጠቁመው፤ ከመጋቢት መጀመሪያ እስከ ሚያዝያ መጨረሻ በጣለው የበልግ ዝናብ 105 ሚሊዮን የሚሆኑ ችግኞች መተከላቸውንና ቀሪው ተከላ በሐምሌ ወር እንደሚቀጥል ገልጸዋል። ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል ጥድ፣ ኮሶ፣ ዋንዛ፣ ዝግባ፣ ግራቪሊያ፣ የእንስሳት መኖና የጥላ ዛፎች የሚገኙበት ሲሆን፣ 8 በመቶ ያህሉ ደግሞ ለሰው ምግብነት የሚውሉ አትክልትና ፍራፍሬ ናቸው ብለዋል። የሐረና ቡሉቅ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ኢብራሂም ሐሰን፤ በወረዳው የህዝቡን የድርቅ ተጋላጭነት ለመከላከል የተጀመረው ጥረት ህብረተሰቡን በማሳተፍ መጠናከሩን ገልጸዋል። በዚህም በ60 በመቶው የበልግ ዝናብ በመጠቀም፣ ለተከላ ከተዘጋጁ 25 ሚሊዮን ችግኞች መካከል ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነውን መትከል መቻሉን አስታውቀዋል። ከወረዳው ነዋሪዎች መካከል አርብቶ አደር ጀማል ሁሴን በሰጡት አስተያየት፤ የድርቅ ተጋላጭነትን ለመቀነስ ችግኝ መትከል የህልውና ጉዳይ መሆኑን ካለፉት ዓመታት ተጨባጭ ውጤት መረዳታቸውንና በዘንድሮው መርሃ ግብር ላይ በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል። በባሌ ዞን ባለፈው የክረምት ወቅት ከተተከሉ ከ245 ሚሊዮን በላይ ችግኞች መካከል በተደረገ ቆጠራ 87 በመቶው ጸድቆ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንደሚገኝ ተገልጿል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለከተማዋ አካባቢ ጥበቃ፣ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው
Jun 16, 2026 357
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 9/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለአጋሮ ከተማ የአካባቢ ጥበቃ፣ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የከተማዋ አስተዳደር ገለጸ። የከተማዋ ወጣቶችም በአረንጓዴ አሻራ ሥራ ላይ በማህበር ተደራጅተው በመስራታቸው ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን ከማሳደጋቸው ባለፈ ለሌሎች ሰዎችም የሥራ ዕድል መፍጠራቸውን ተናግረዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኞችን በማፍላትና በመትከል እንዲሁም በመንከባከብ የጽድቀት መጠናቸውን በማሳደግ ካላቸው ሁሉ አቀፍ ጥቅም በተጨማሪ ለመጪው ትውልድ እንዲተላለፉ ማድረግ ይጠበቃል። በመሆኑም ህብረተሰቡ ልክ እንዳለፉት ጊዜያት ሁሉ ዘንድሮም በችግኝ ተከላው ተሳትፎውን በማጠናከር አረንጓዴ፣ ጤናማ እና ዘላቂ ሕይወት ያለው አካባቢ ለመፍጠር መሥራት ይገባዋል። የአጋሮ ከተማ ነዋሪዎች ቀደም ባሉት ጊዜያት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የችግኝ ተከላ ሥራው ላይ በንቃት በመሳተፋቸው ተጠቃሚነታቸው ማደጉ ተመላክቷል። ዘንድሮ በሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ላይም በንቃት እና በተደራጀ አግባብ በመሳተፍ ተጠቃሚነታቸውን ይበልጥ ለማሳደግ እንደሚሰሩ ተገልጿል። የአጋሮ ከተማ ግብርና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እንዳለ ማመጫ እንደገለጹት፣ በከተማዋ ባለፉት ዓመታት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ገብር ላይ ህብረተሰቡን በስፋት በማሳተፍ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል። በዚህም ለከተማዋ አካባቢ ጥበቃ፣ ለኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው ሲሉም ገልጸዋል። በዚህም ህብረተሰቡ ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ ተጠቃሚነቱን እያረጋገጠ መሆኑ በተጨባጭ መታየቱን ጨምረው ተናግረዋል። በዘር ዝግጅት፣ ችግኝ በማፍላት፣ በመጓጓዣ፣ በተከላ፣ በደን እንክብካቤ እና በአካባቢ ጥበቃ ዘርፎች ላይ ለበርካታ ሰዎች የአጭርና የረጅም ጊዜ የሥራ ዕድሎች መፍጠር መቻሉንም አክለዋል። ዘንድሮ ለሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ የተለያዩ ዝርያዎች ያላቸው ችግኞች ዝግጅት መከናወኑንም ጠቁመዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አረንጓዴ ኢኮኖሚን ከመገንባትና አካባቢን ከማስዋብ ባሻገር የሥራ ዕድል በመፍጠር የህብረተሰቡን ኑሮ ለማሻሻል ከፍተኛ ሚና እንዳለውም በሥራው ላይ የተሳተፉ የከተማዋ ነዋሪዎች ገልጸዋል። በዘርፉ ተሰማርተው ውጤታማ ከሆኑ ወጣቶች መካከል ፈሪድ ነዚፍ እንደተናገረው፣ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ላይ በማህበር ተደራጅተን በመስራታችን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታችን ከማደጉ ባለፈ ለሌሎች ሰዎችም የሥራ ዕድል መፍጠር ችለናል ብሏል። ወጣት ኑሬ አባ ጀባል በበኩሉ፣ በማህበር ተደራጅተው በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በሚሰሩት የ"grafting" (የተክል ማጣመር) ሥራን በመሥራትና በመሸጥ ቤተሰባችንን እያስተዳደርን እንገኛለን ሲል ገልጿል። ሌላኛው ወጣት ምርጋኒ አባ ፊጣ በበኩሉ፣ በማህበር ተደራጅተን በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት ላይ በመሳተፍ ተጠቃሚነታችን እያደገ ነው ብሏል። በአረንጓዴ አሻራ ዘርፍ ላይ በምንሰራው ስራ ሁሉ የከተማ አስተዳደሩ ድጋፍ አልተለየንም ያለው ወጣት ምርጋኒ ለወጣቶችና ለሴቶች ሰፊ የሥራ ዕድል በመፍጠር ገቢያቸው እንዲሻሻል እያደረገ ይገኛል ሲል ተናግሯል።
አረንጓዴ ዐሻራ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ብልፅግና አሰናስሎ የሚያረጋግጥ ወሳኝ የልማት አቅጣጫ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jun 15, 2026 1042
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ብልፅግና አሰናስሎ የሚያረጋግጥ ብሔራዊ የልማት አቅጣጫ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያ ኮፕ-32ን ስታስተናግድ 65 ቢሊየን ችግኞችን መትከል የቻለች ሀገር መሆኗን ለዓለም እናበስራለንም ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር "ተስፋን እንትከል" በሚል መሪ ሀሳብ በቢሾፍቱ ሆራ አርሰዲ ሐይቅ ዳርቻ አስጀምረዋል። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ፣ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አገኘሁ ተሻገር፣ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የፌዴራልና የክልል መንግሥታት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የዘንድሮው አረንጓዴ ዐሻራ ማስጀመሪያ በቢሾፍቱ ከተማ መካሄዱ ከተማዋ ከራሷ አልፎ ለአዲስ አበባና ሌሎች ከተሞች ችግኞችን የምታመርት መሆኗን ዕውቅና የሚሰጥ ነው። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነትና ብልፅግና አሰናስሎ የሚያረጋግጥ ብሔራዊ ኢኒሼቲቭ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ አረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር የደን፣ የሰብልና ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት የማረጋገጥ ወሳኝ የልማት አቅጣጫ መሆኑን አስረድተዋል። የአንድ ሀገር ሉዓላዊነት የሚደፈረው በሁለት ጉዳዮች ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ አንዱ ባዕዳን ኃይሎች አልመውና ድንበር ጥሰው ሲገቡ ሲሆን፤ ሌላኛው የእኛ ሃብትና ንብረት በዋዛና ፈዛዛ ሲወጣም የሉዓላዊነት መደፈር ነው ብለዋል። ኢትዮጵያም ባለፉት ዓመታት ያጣችው የአፈር መጠን በገንዘብ ሊተመን የማይችል ከፍተኛ ጉዳት ማድረሱን ገልጸዋል። የእኛ አባቶች ዓድዋ ላይ ወራሪን በማሳፈር ገድል ሠርተዋል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፤ የእኛ ትውልድም በአረንጓዴ ዐሻራ ሌላኛውን ለትውልድ የሚሻገር ታላቅ ገድል እየሰራ ነው ብለዋል። የዘንድሮው "ተስፋን እንትከል" መሪ ሃሳብ የነገን ብሩህ ዛሬ በመፃፍ፣ የተስፋ ስሮች ዘልቀው የብልፅግና ግንድ፣ ቅርንጫፍና ፍሬ ተስፋፍቶ ሃብት እንዲሆኑ የሚያመላክት መሆኑንም ተናግረዋል። የተስፋ ምርጫም የቢሾፍቱ ከተማ ነዋሪዎችና መላው ኢትዮጵያውያን በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የትኛውም የአየር ሁኔታ ሳይበግራቸው ተስፋን በመሰነቅ ድምፅ መስጠታቸውን ከመሪ ሃሳቡ ጋር አሰናስለው አስገንዝበዋል። ተስፋ የአረንጓዴ መቀነት ነው፣ ሀገርን ያለብሳል፣ የተራቆተና የገረጣን መሬትም ያለመልማል፣ ተስፋ አረንጓዴ ፀዳልና መንፈስን የሚያድስ አረንጓዴ ወርቅ ነው ብለዋል። በተጨማሪም የአረንጓዴ ውርስ ትውልድ የሚከበርበት ቀጣዩ ትውልድ ልምድና ባህል የሚያደርገው የብልፅግና መሠረት መሆኑን ገልጸዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ በመደመር መርህ የኢትዮጵያን የተረጂነት ታሪክ ወደ ማድረግ ዘመን የሚያሸጋግር መሆኑን አንስተው፤ መርሃ ግብሩ አፈራችንን ከስደት፥ ግድባችንን ከደለል የሚታደግ ስኬታማ የልማት ዓምድ ነው ብለዋል። ከአስር በላይ አዳዲስ የፍራፍሬ ዝርያዎችን በኢትዮጵያ በማላመድ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚያስችል ስራ እየተሰራ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ለዚህ ስኬትም ሁሉም ሊረባረብ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ በችግኝ ማፍላት፣ በእንክብካቤ፣ በመትከል፣ በችግኝ ሽያጭ፣ በንብ ማነብና በእንስሳት ማድለብ ለበርካታ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠሩን አብራርተዋል። በቀጣይም የበለፀገች ኢትዮጵያን ለትውልድ ለማስተላለፍ በሁሉም መስክ የተመዘገበውን ስኬት ማስፋትና ማስቀጠል እንደሚያስፈልግም አፅንኦት ሰጥተዋል። ከ2011 ዓም ጀምሮ በተከናወነ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ከ48 ቢሊየን በላይ ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ያላቸው ችግኞች መተከላቸውን ጠቁመው፥ ዘንድሮም ከስምንት ቢሊየን በላይ ችግኝ በመትከል በአጠቃላይ 56 ቢሊየን እንደሚደርስ አስታውቀዋል። ኢትዮጵያ ኮፕ-32ን ስታስተናግድ 65 ቢሊየን ችግኞችን መትከል የቻለች ሀገር መሆኗን ለዓለም እናበስራለን ብለዋል። ለዚህም ሁሉም ዜጋ የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ዐሻራ ስኬት በማስቀጠል በቁርጠኝነት መስራት እንዳለበት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥሪ አቅርበዋል። በሚቀጥሉት የክረምት ወራትም "ተስፋን በመትከል" በዓድዋ ድል ቅድመ አያቶች የተቀዳጁትን ድል በአረንጓዴ አሻራ ልማት በመድገም የኩራት ምንጭ የሆነች ኢትዮጵያን ለትውልድ ማስተላለፍ እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ ብሔራዊ ሥራችን ከተፈጥሮ የመታረቅ በልማት የመላቅ አዲስ ጎዳና ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Jun 15, 2026 822
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018(ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ ዐሻራ ብሔራዊ ሥራችን ከተፈጥሮ የመታረቅ በልማት የመላቅ አዲስ ጎዳና ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው እንደገለጹት ለአንዲት ኢትዮጵያ እንደ አንድ ሕዝብ ተደምረን በሠራነው የአረንጓዴ ዐሻራችን፣ ልምላሜ የተራቡ ተራሮች አረንጓዴ ለብሰዋል ብለዋል። ምንጮች እና ተፋሰሶች ምድሩን አረስርሰዋል ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በረሃማነት ይጸናባቸው የነበሩ ክበበ ምድሮች ነፋሻማ ሆነዋል ሲሉም ገልጸዋል። የተፈጥሮን ጫና ተቋቁመናል! ይህ ደግ የተፈጥሮ ዕርቅ ነው ሲሉም ተናግረዋል በመልዕክታቸው። የምግብ ሉዓላዊነት ማረጋገጥን ከተፈጥሮ ጥበቃ ጋር በማስተሣሠር በተሠራው ሥራ የፍራፍሬ ተክሎች በስፋት ለምተዋል፤ ፍሬ መስጠትም ጀምረዋል ብለዋል። ይህም በምግብ ራስን ለመቻል ለጀመርነው ብሔራዊ ኢኒሼቲቭ ተደማሪ ዐቅም ሆኗል ሲሉም ተናግረዋል። አረንጓዴ ዐሻራ የኢትዮጵያ ልጆች ከፖለቲካ አሰላለፍ አልፈው፣ ከሐሳብ ተቃርኖ ተሻግረው፣ ገጸ ብዙ ልዩነቶችን አሸንፈው ለሀገርና ለትውልድ አስበው ያሳኩት የመተባበር ድል፣ የተጨበጠ ማሳያ ነው ሲሉ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ልጆች ስንተባበር ትርፋችን እልፍ፣ ዕቅዳችንም የተሳካ የሠመረ ይሆናል ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የዘንድሮ የአረንጓዴ ዐሻራ የእስከ ዛሬ ድካማችን መደምደሚያ፣ የድላችን መዳረሻ፣ በድል ላይ ቆመን ለሌላ የላቀ ድል የምንነሣበት ልዩ ዓመት ነው ብለዋል። ሁላችንም በሩጫ ትግል ሊያልቅ ሲል እንደሚበረቱት ሊጠናቀቅ ሲል እንደሚፈጥኑት ጀግኖች አትሌቶቻችን ካለፉት ዓመታት አስበልጠን እንትከል! እንበርታ! እንፍጠን ሲሉም ጥሪ አቅርበዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር በይፋ አስጀመሩ
Jun 15, 2026 526
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 8/2018 (ኢዜአ):- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር ዛሬ በይፋ አስጀምረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት በዚህ ዓመት 8 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ግብ አስቀምጠን፣ ከፍ ወደ አደረግነው 65 ቢሊዮን ችግኞች ግብ የመድረስ ትልማችንን ለማሳካት በጽናት እየገሰገስን እንገኛለን ብለዋል። ንቅናቄውን ተቀላቅለው ለመጭው ትውልድ አረንጓዴ ዐሻራዎን ያኑሩ ሲሉም ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
ከጤና ጠንቅነት ወደ ንጹህ ውብ መዝናኛ ስፍራነት የተለወጠው የወንዝ ዳርቻ ልማት
Jun 14, 2026 812
ከእንጦጦ እስከ ፒያሳ የተዘረጋው የወንዝ ዳርቻ ልማት ቀደም ሲል የቆሻሻ መጣያና ለጤና ጠንቅ የነበሩ አካባቢዎችን ወደ አረንጓዴ፣ የንግድና የመዝናኛ ማዕከልነት በመቀየር የነዋሪዎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ያረጋገጠ ስኬታማ ሥራ መሆኑን ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ ከእንጦጦ እስከ ፒያሳ (ቀጨኔ መድኃኔዓለም) የተዘረጋው የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት፣ የአዲስ አበባን ገጽታ ከመቀየርና የነዋሪዎቿን የኑሮ ጥራት ከማሻሻል አንጻር እጅግ ሰፊና ዘርፈ-ብዙ ትርጉም ያለው ግዙፍ ስራ ነው። ቀደም ሲል እነዚህ የወንዝ ዳርቻዎች የፍሳሽና የደረቅ ቆሻሻ መጣያ፣ እንዲሁም ለከባድ ጠረንና ለበሽታ መፈልፈያነት የተጋለጡ ነበሩ። ይህ ፕሮጀክት ግን የወንዝ ዳርቻዎቹን በማጽዳትና የተፈጥሮ ፍሰታቸውን ጠብቀው እንዲፈሱ በማድረግ የስነ-ምህዳር መዛባትን ታድጓል። ፕሮጀክቱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ አረንጓዴ ተክሎች፣ አበቦችና ዛፎች በመተከላቸው አካባቢው ንጹህ አየር እንዲኖረውና የሙቀት መጠንን ለመቀነስ ትልቅ አስተዋጽኦ አድርጓል። የእግር ጉዞ መስመሮች እና የብስክሌት መንገዶች ነዋሪዎች የአካል ብቃት እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ ምቹ ዕድል ፈጥረዋል። ቤተሰቦችና ጓደኛማቾች የሚገናኙባቸው፣ የተለያዩ ማህበራዊና ባህላዊ ሁነቶች የሚስተናገዱባቸው ሰፊና ውብ ስፍራዎች ተፈጥረዋል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ልማቱ ከመጀመሩ በፊት የነበረውን አስቸጋሪ ሁኔታ በማስታወስ አሁን የመጣውን ለውጥ አስደሳችና የሚስደንቅ መሆኑን ይናገራሉ። ወይዘሮ አስናቀች ካሳ እንደገለጹት ፤ የወንዝ ዳርቻ ልማቱ ከመሰራቱ በፊት አካባቢው ንጽህናው የተበላሸ፣ የቆሻሻ መከማቻ እና ለጤና የማይበጅ ነበር። አሁን ግን ሙሉ በሙሉ ተቀይሮ እጅግ መልካም ገጽታን መላበሱን ልማቱ የአካባቢውን ንጽህና ከመጠበቅ ባለፈ፣ ለልጆች መጫወቻነት፣ ለአዋቂዎች መዝናኛነት እና ለሥራ ዕድል መፍጠሪያነት እየዋለ ይገኛል ብለዋል፡፡ ሌላኛው የአካባቢው ነዋሪ አቶ ኪዳነቃል እርጌ በበኩላቸው፤ የወንዝ ዳርቻ ልማቱ ለአካባቢው ሰላምና ጸጥታ መከበር ጉልህ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ከዚህም በተጨማሪ በልማቱ አማካኝነት በርካታ መንገዶች በመገንባታቸው ለነዋሪዎች ምቹና አማራጭ የትራንስፖርት ዕድል መፍጠሩን አስታውቀዋል። ፕሮጀክቱ የያዛቸው ዘርፈ-ብዙ መሰረተ-ልማቶች ሕፃናትን፣ ወጣቶችንና ወላጆችን ታሳቢ ያደረጉ እንዲሁም ሁሉንም የሕብረተሰብ ክፍሎች ያካተቱ ሆነው መገንባታቸው ልዩ ያደርገዋል ስትል የተናገረችው ወጣት አዳነች አይሳ ናት። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ ኃይሌ ሰለሞን ከልማቱ በፊት በአካባቢው የወንዝ መሻገሪያ ድልድይ ባለመኖሩ እና በቆሻሻ ሽታ ሳቢያ በእጅጉ ይችገሩ እንደነበር ተናግረው ፤አሁን ግን የአካባቢው ገጽታ ተስተካክሎ ለሌሎች ሰዎች ጭምር ተመራጭ መዝናኛ ሆኖ በመገኘቱ ታላቅ ደስታ ይሰማኛል ሲሉ ገልጸዋል።
በዞኑ የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ ለኑሮ ተስማሚ እና ለጤና ምቹ አካባቢዎችን እየፈጠረ ነው
Jun 14, 2026 620
ወልቂጤ ፤ ሰኔ 7/2018(ኢዜአ)፦ በጉራጌ ዞን "ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ ለኑሮ ተስማሚ እና ለጤና ምቹ አካባቢዎችን እየፈጠረልን ነው ሲሉ የዞኑ ነዋሪዎች ገለጹ። በጉራጌ ዞን ጌታ ወረዳ ኸምብያቴ ቀበሌ የፅዱ መንደር እውቅና የተሰጠ ሲሆን የፅዱ ኢትዮጵያ መስፈርትን ያሟሉ አካባቢዎች እና ግለሰቦች ቤት ምልከታ ተደርጓል ። የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ በሀገሪቱ የቆሻሻ አወጋገድ ስርዓትን ለማሻሻል፣ የገጠርና የከተሞችን ውበት ለመጠበቅ እና ለዜጎች ምቹ የመኖሪያ አካባቢን ለመፍጠር ያለመ ሀገራዊ ዘመቻ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተጀመረው ኢንሼቲቭ በሁሉም የሀገሪቷ አካባቢዎች ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑ ይታወቃል። በጉራጌ ዞን ጌታ ወረዳ የኸምብያቴ ቀበሌ ነዋሪዋ ወይዘሮ ዓመቱ ብዙ የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ መተግበር የውሀ ብክለትን በመከላከል፣ የፅዳት ዘመቻና የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ስራዎችን ወጥ በሆነ መልኩ ለመተግበር እንዳስቻላቸው ጠቅሰዋል። ደጃቸው፣ ቤታቸውንና ጓሮአቸው ፅዱ እና ውብ ማድረጋቸውን ጠቁመው ይህም በጤናቸው እና በኑሮቸው ተጠቃሚ እንዳደረጋቸው ተናግረዋል። ሌላኛው አቶ ገብሬ ዛጋ የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ የተሻለ መፀዳጃ ቤት እንዲጠቀሙ በማድረጉ ከንፅህና ጉድለት የሚመጣ በሽታን ለመከላከል እንዳስቻላቸው ገልፀዋል። የተፈጠረውን ግንዛቤ እና ስልጠና ቀጣይነት ባለው መልኩ እንደሚተገብሩት ተናግረዋል። የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ የአካባቢ ጽዳትና ውበትን በጋራ በመጠበቅና በመንከባከብ ምቹና ተመራጭ አኗኗርን ፈጥሮልናል ያሉት ደግሞ ወይዘሮ ክብነሽ ፉጃጋ ናቸው ። አካባቢያችንን ፅዱ እና ለመኖሪያ ምቹ በማድረግ ረገድ እንዲሁም ተስማሚ መንደርን በመፍጠር በኩል በቅንጅት መስራታችን ለውጤት አብቅቶናል ብለዋል። የጌታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ በህሩ ኸይረዲን የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ ከብክለት የፀዳ ወረዳን እውን ለማድረግ አስቻይ ሁኔታዎችን መፍጠሩን አንስተዋል። ጤናው የተጠበቀ ማህበረሰብ ለመፍጠር የተሰራው ስራ የእናቶች ወሊድ ክትትልና አገልግሎት ሙሉ በሙሉ በህክምና ተቋማት ለማድረግ አስችሏል ብለዋል። በወረዳው የሚገኙ የጤና፣ የትምህርት፣ የእምነት እና ሌሎችም ተቋማት ጭምር ፅዱና ምቹ እየተደረጉ መሆናቸውን አንስተው እውቅና ለተሰጣቸው ፅዱ ቀበሌዎች ጠንካራ ክትትልና ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል። የጉራጌ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ አየለ ፈቀደ የ"ፅዱ ኢትዮጵያ" ንቅናቄ በዞኑ ህዝብ ጤና እና አኗኗር ላይ ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ በመሆኑ ተጠናክሮ እንዲተገበር አድርጎታል ብለዋል። እስካሁን በዞኑ ከሚገኙ 315 ቀበሌዎች መካከል 87 በመቶ ያህሉ የዚህ ኢንሼቲቭ ትግበራ ተጠቃሚዎች መሆን መቻላቸውንም ለአብነት አስረድተዋል። መርሃ ግብሩ የተሻሻሉ መፀዳጃ ቤቶችን በመገንባት የሰውና የእንስሳት መኖሪያን በመለየት ተላላፊ በሽታዎችን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር እያስቻለ በመሆኑ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
በክልሉ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማትን ስኬታማ ለማድረግ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ይጠናከራሉ
Jun 13, 2026 805
ጋምቤላ፤ ሰኔ 6/2018(ኢዜአ)፦ በክልሉ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማትን ስኬታማ ለማድረግ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ይጠናከራሉ ሲሉ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። የአኙዋሃ ባዮስፌር ሪዘርቭ በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) መመዝገቡን በማስመልከት የዕውቅና መርሃ ግብር ዛሬ በአኙዋሃ ዞን አቦቦ ወረዳ ተካሂዷል። ርዕሰ መስተዳድሯ በወቅቱ እንደገለጹት በክልሉ ዘላቂ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት እውን ለማድረግ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ይጠናከራሉ። በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች በርካታ ስኬቶች መመዝገባቸውን አስታውሰዋል። በተለይም በአረንጓዴ አሻራ ልማት መርሃ ግብር በተከናወኑ ስራዎች የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ በማድረግ የተፈጥሮ ሚዛን በማስጠበቅበኩል ውጤታማ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ነባር የተፈጥሮ የደንና የብዝሃ ህይወት ሀብትን በመጠበቅ ለዘላቂ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እንዲውል በማድረግም አበረታች ስኬተቶች ተመዝግበዋል ብለዋል። ለዚህም ዋነኛ ማሳያው እውቅና የተሰጠው የአኙዋሃ ባዮስፌር ሪዘርቭ ጨምሮ የማጃንግ የተፈጥሮ ደን በተባበሩት መንግስታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት መመዝገባቸውን ጠቅሰዋል። በክልሉ በሁለቱ ዞኖች በባዮስፌር ሪዘርቭነት የተመዘገቡት ጥብቅ የተፈጥሮ ደኖች የአየር ንብረት ሚዛንን ከመጠበቅ ባለፈ ለቱሪዝም ኢንዱስትሪው ልማት የላቀ አብርክቶ ያላቸው መሆኑን አመልክተዋል። በመሆኑም የደን ሀብቶችን በመጠበቅና በመንከባከብ ለዘላቂ ልማት ለመዋል በሚደረገው ጥረት የህብረተሰቡ ተሳትፎ ሊጠናከር እንደሚገባ ርዕሰ መስተዳደሯ አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ብዝሃ ህይወት ኢንስቲትዩት ተወካይ አቶ አበራ ስዩም በበኩላቸው የአኙዋሃ ጥብቅ ደን በባዮስፌር ሪዘርቭ መመዝገቡ ኢትዮጵያ ለብዝሃ ህይወት ሀብት ጥበቃ ያላትን ቁጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል። በዞኑ በባዮስፌር ሪዘርቭ የተመዘገበው ጥብቅ ደን የተፈጥሮ ስነ-ምህዳርን በመጠበቅ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚን መገንበት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የመልካ ኢትዮጵያ ዋና ዳይሬክትር ሰለሞን ከበደ እንዳሉት የአኙዋሃ ጥብቅ ደን በባዮስፌር ሪዘርቭነት በዩኔስኮ ሊመዘገብ የቻለው በውስጡ በያዛቸው እምቅ የእንስሳትና የዕፅዋት ብዝሃ ህይወት ሀብቶች ነው ብለዋል። የተመዘገበው ጥብቅ ደን ለሀገር ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል። በዞኑ በባዮስፌር ሪዘርቭ የተመገበው ጥብቅ የተፈጥሮ ደን ለክልሉ ብቻ ሳይሆን ለሀገር ኢኮሚኖሚ ግንባታ አስተዋጽኦው የጎላ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የአኙዋሃ ዞን አስተዳደሪ አቶ ኝኬው ጊሎ ናቸው። የአኙዋሃ ባዮስፌር ሪዘርቭ በዩኔስኮ የተመዘገበ ሲሆን በውስጡ ከአንድ ሺህ በላይ የዕፅዋት፣ 327 የአእዋፍ፣ 69 የአጥቢና 17 የተሳቢ እንስሳት ዝርያዎችን እንደያዘ በስነ-ስርዓቱ ላይ ተገልጿል።
የአረንጓዴ አሻራ ልማት አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ የምግብ ዋስትና መሠረት እየሆነ ነው
Jun 13, 2026 550
ጭሮ፤ ሰኔ 6/2018 (ኢዜአ)፦ የአረንጓዴ አሻራ ልማት አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ የምግብ ዋስትና መሠረት እየሆነን ነው ሲሉ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሐረርጌ ዞን በዘርፉ ልማት ተጠቃሚ የሆኑ አርሶ አደሮች ተናገሩ። በምዕራብ ሐረርጌ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ልማት መርሐ ግብር ከ396 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑንም የዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ጽሕፈት ቤት አስታውቋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት ለተለያዩ ጥቅሞች የሚውሉ ችግኞች ተተክለው ለስኬት በቅተው ዘርፈ ብዙ ጥቅም በመስጠት ላይ ይገኛሉ። ከዚሁ ጋር በተገናኘ የኢዜአ ሪፖርተር ያነጋገራቸው አርሶ አደሮች በአረንጓዴ አሻራ ልማት ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እያገኙ መሆኑን ገልጸዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል አርሶ አደር ዘሪሁን ከበደ እና አርሶ አደር መልካሙ ተስፋዬ፣ በአረንጓዴ አሻራ በየዓመቱ የተከሏቸው ችግኞች የተራቆቱ አካባቢዎችን ከመሸፈን ባለፈ የገቢ እና የምግብ ምንጭ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአረንጓዴ አሻራ ችግኝ መትከል ከጀመሩ ወዲህ የመሬት ለምነትና እርጥበት እንዲጠበቅ ማስቻሉን አንስተው፤ በፍራፍሬ ልማት የተተከሉ ችግኞችም ጥቅም እየሰጡ ነው ብለዋል። በመሆኑም የአረንጓዴ አሻራ ልማት አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ የምግብ ዋስትና መሠረት እየሆነን ነው ሲሉ ተናግረዋል። በዞኑ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ጽሕፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት ልማት ቡድን መሪ አቶ ዋሴ በቀለ፤ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ሥራዎች በብዙ መልኩ ጥቅም እየሰጡ መሆኑን አንስተዋል። አካባቢን ከመጠበቅ ባለፈ የምግብ ዋስትና መሠረት እና ጥሩ የገቢ ምንጭም እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል። በመሆኑም ዘንድሮም ለችግኝ ተከላው የተቀናጀ ዝግጅት መደረጉን አንስተው፣ በመርሐ ግብሩ ከ396 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ለችግኝ ተከላውም ከ76 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ዝግጁ መሆኑን አንስተው፣ ዕቅዱን ለማሳካት የሁላችንም ዝግጁነት ሊኖር ይገባል ብለዋል። የዞኑ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ኃላፊ ተወካይ አቶ ፍጹም አማረ፤ በዞኑ ችግኞችን ከመትከል ባለፈ በጥበቃና እንክብካቤ ዙሪያም የታየው ተሳትፎ የልማት ሥራውን ለውጤት አብቅቶታል ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሩ የደን ሀብት መጠንን ከመጨመር ባለፈ፣ ለምግብ ዋስትና መሠረት እያኖረ እና አይነተኛ የሥራ ዕድልም ሆኗል ሲሉ ተናግረዋል።
ከስምንት ቢሊዮን በላይ ችግኞች ለተከላ ዝግጁ ሆነዋል- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jun 13, 2026 344
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6 /2018 (ኢዜአ)፦ ለዘንድሮው የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ከስምንት ቢሊዮን በላይ ችግኞች ለተከላ መዘጋጀታቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ወቅት ላይ እንገኛለን ብለዋል። ለዚህም ከስምንት ቢሊዮን በላይ ችግኞች ዝግጁ መደረጋቸውንም ገልጸዋል። አረንጓዴ ለሆነች ነገ፤ ሁላችንም ተስፋን እንትከል በማለትም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥሪ አቅርበዋል።