አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በክልሉ በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መረሃ ግብር ከ17 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የቡና እና የፍራፍሬ ችግኝ ተተክሏል
Aug 20, 2025 12
ባሕርዳር፤ነሐሴ 14/2017 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል በክረምቱ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር 17ሺህ 650 ሄክታር መሬት ላይ የቡና እና የፍራፍሬ ችግኝ በመትከል እየለማ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የአትክልትና ፍራፍሬ ባለሙያ አቶ አወቀ ዘላለም ለኢዜአ እንደገለጹት፥ በክልሉ የቡና እና የፍራፍሬ ልማትን በማስፋፋት የአርሶ አደሩን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ ነው። በዚህም በተያዘው ክረምት 17 ሺህ 650 ሄክታር መሬት ላይ የቡና፣ የተለያየ የቆላ እና የደጋ ፍራፍሬ ችግኝ በመትከል እየለማ መሆኑን ገልጸዋል። ከተተከለው ችግኝ ውስጥም ከቡና ሌላ አቦካዶ፣ ማንጎ፣ ፓፓያ፣ ሙዝ፣ ዘይቱን፣ ሎሚ፣ አፕል እና ኮክ እንደሚገኝበት ጠቅሰዋል። ተከላው የተካሄደው 354 ሺህ 841 አርሶ አደሮችን በማሳተፍ መሆኑን ጠቁመው፤ የተተከለው ችግኝ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ብልጫ አለው ብለዋል። በዘንድሮው የችግኝ ተከላ ለፍራፍሬ ልማት ምቹ መሆናቸው በተለዩ 36 ወረዳዎች በኩታ ገጠም መካሄዱን አንስተው፤ ይህም ተባይና አረምን በጋራ በመከላከል ምርታማነትን የሚያሳድግ መሆኑን ገልጸዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የጃቢጠህናን ወረዳ አርሶ አደር ተፈራ መልስ በሰጡት አስተያየት፤ ዝርያው የተሻሻለ የቡና ችግኝ በአንድ ሄክታር ተኩል መሬት ተክለው እያለሙ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም እስከ ሶስት ዓመት ባለው ጊዜ ውስጥ ምርት የሚሰጥ መሆኑን ያመለከቱት አርሶ አደሩ፤ ችግኙን መንከባከብና ያረጀውን ጎንድለው በማደስ የተሻለ ምርት በመሰብሰብ ተጠቃሚ ለመሆን በባለሙያ ታግዘው እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ውበት ተስፌ፤ቀደም ሲል በሩብ ሄክታር ካለሙት የቡና ተክል ያገኙት ምርት ሸጠው ተጠቃሚ መሆናቸውን አውስተዋል። ያገኙትን ለማስፋትም በተያዘው ክረምት ተጨማሪ የቡና ችግኝ አዘጋጅተው እየተከሉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በአንድ ሄክታር መሬት እያከናወኑት ያለው የቡና፣ አቦካዶና ማንጎ ልማት ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን የገለጹት ደግሞ በሰሜን ጎጃም ዞን የሰሜን ሜጫ ወረዳ አርሶ አደር ነጋ ታደለ ናቸው። ከግብርና ቢሮው የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው፤በአማራ ክልል ከ91 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት በቡናና ፍራፍሬ ተክል ለምቶ ይገኛል።
ከቃል ኪዳን ወደ ተግባር፤ የናይሮቢ እና አዲስ አበባ ጉባኤዎች ትስስር
Aug 18, 2025 171
አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ ውይይቶችና መድረኮች ላይ በጋራ ድምጿን የማሰማት አቅሟን እያሳደገች ይገኛል። እ.አ.አ በ2023 በኬንያ ናይሮቢ የተካሄደው የመጀመሪያው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ የዚሁ በአንድነት የመቆም ዋነኛ ማሳያ ነው። በናይሮቢው ጉባኤ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ፣ የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዝዳንት ኡርሱላ ቮን ደር ሌይን እና የዓለም ተጽእኖ ፈጣሪ ግለሰቦችን ጨምሮ ከ30 ሺህ በላይ ተሳትፈዋል። በጉባኤው “የናይሮቢ ድንጋጌ” በሚል 11 ነጥቦችን የያዘ የአቋም መግለጫ ወጥቷል። የድንጋይ ከሰል በኃይል አማራጭነት የሚጠቀሙ ሀገራትና ተቋማት፣ በአቪዬሽንና የማሪታይም ትራንስፖርት ላይ ዓለም አቀፍ የካርቦን ታክስ መጣል አለበት የሚለው ጉዳይ በቀዳሚነት የሚጠቀስ ነው። ዓለም አቀፍ የፋይናንስ መዋቅርን በማማሻል ለአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ ያለውን አቅርቦት ማሳደግ፣ የአፍሪካን የታዳሽ ኃይል አቅም እ.አ.አ በ2030 300 ጊጋ ዋት ማድረስ፣ አፋጣኝ የአየር ንብረት ለውጥ እርምጃዎች፣ የጉዳት ካሳ ክፍያ ፈንድ፣ ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስራ የእዳ እፎይታ ማድረግ፣ የማይበገር አቅም መገንባት፣ የአፍሪካ የተፈጥሮ ሀብቶች ከአየር ንብረት ጥበቃ ጋር አጣጥሞ መጠቀም፣ ቀጣናዊ ትብብርን ማጠናከር እንዲሁም የወጣቶችና ሴቶች አካታችነት ማሳደግ የአቋም መግለጫው ያተኮረባቸው ሌሎች ነጥቦች ናቸው። ለጋሾች 26 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ድጋፍ ለማድረግ ቃል የገቡ ሲሆን የአፍሪካ ልማት ባንክ እ.አ.አ 2025 ማብቂያ ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል የሚያደርገውን የፋይናንስ ድጋፍ ወደ 23 ቢሊዮን ዶላር ለማሳደግ ቃል ገብቶ ነበር። የናይሮቢው ጉባኤ ነጥቦች አፍሪካ በተሳተፈችባቸው የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ መድረኮች ላይ በጋራ ድምጿን እንድታሰማ ትልቅ አቅም ፈጥሯል። በተለይም የካርቦን ታክስ፣ የሴቶች እና ወጣቶች አካታችነት፣ የታዳሽ ኃይል ምንጮን መጨመርና ቀጣናዊ ትብብርን ማጠናከር ዓለም አቀፍ ትኩረት እንዲያገኙ አስችሏል። ይሁንና ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ ቃል ኪዳኖች በሚገባ አለመፈጸም፣ የካርቦን ታክስ ሀሳቦችን ወደ ተጨባጭ የተግባር ፖሊሲ የመቀየር ፈተና፣ የእዳ እፎይታን በሚፈለገው ደረጃ አለማግኘት እና ተጋላጭ የህብረተሰብ ክፍሎች የኃይል አቅርቦት ተደራሽነት በዋናነት የሚጠቀሱ ፈተናዎች ናቸው። ከናይሮቢው ጉባኤ በኋላ የነበሩ ስኬቶች እና ማነቆዎች በአዲስ አበባ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም የሚካሄደውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ አጀንዳን የቀረጹ ናቸው። የአዲስ አበባው ጉባኤ በኢትዮጵያ እና በአፍሪካ ህብረት የጋራ አዘጋጅነት የሚካሄድ ነው። ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፥ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" የጉባኤው አበይት መሪ ሀሳብ መሆኑን የፕላንና ልማት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ጉባኤው የናይሮቢ ድንጋጌን እንደ አሻራ በመጠቀም በአየር ንብረት ለውጥ ቃል የተገቡ ጉዳዮች ወደ ተግባር መቀየር ላይ ዋነኛ ትኩረቱን አድርጎ ይመክራል። አፍሪካ በአንገብጋቢው አህጉራዊ ጉዳይ ላይ የመሪነት ሚናዋን ማሳደግ በምትችልበት ሁኔታ ላይም ምክክር ይደረጋል። በጉባኤው በአየር ንብረት ለውጥ መከላከል እና መቆጣጠር ላይ በአህጉር አቀፍ እና በሀገራት ደረጃ የተከናወኑ ስራዎች ይገመገማሉ። ለሰው ልጆች ፈተና የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥ መከላከልና መቋቋም የሚያስችሉ ውሳኔዎች የሚተላለፉበት ትልቅ ጉባኤ እንደሆነም እየተገለጸ ይገኛል። ጉባኤው አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከልና ለመቋቋም በምታደርገው ጥረት ቅድሚያ የምትሰጣቸውን ጉዳዮች አቅጣጫ ለማስያዝ እንደሚረዳም ተመላክቷል። አፍሪካ ለአየር ንብረት ብክለት የምታበረክተው አስተዋጽኦ አነስተኛ ቢሆንም በሚደርሰው ተጽዕኖ ግን ከፍተኛ ተጎጂ መሆኗን የገለጸው የአፍሪካ ህብረት ጉባኤው የአፍሪካ ሀገራት ፍትህን እንደሚጠይቁ አስታውቋል። አፍሪካ መር የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄዎችም ይቀርባሉ። የከፍተኛ ደረጃ ምክክሮች፣ የሚኒስትሮች ውይይት፣ አውደ ርዕዮች፣ የወጣት ፎረሞች እና የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስራን የሚያሳዩ ቀጣናዊ መካነ ርዕይ(ፓቪሊዮኖች) የጉባኤው አካል ናቸው። ኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እየወሰደችው ያለው እርምጃና ለአየር ንብረት ተስማሚ የሆነ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመፍጠር እያከናወነች ያለው ስራ በጉባኤው በተሞክሮነት ታቀርባለች። በብራዚል ቤለም በሚካሄደው 30ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ(ኮፕ 30)፣ በአሜሪካ ኒው ዮርክ በሚካሄደው 80ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ፣ በደቡብ አፍሪካ ጆሃንስበርግ ለሚካሄደው የቡድን 20 አባል ሀገራት ጉባኤ እና ሌሎች ዓለም አቀፍ ሁነቶች ላይ የሚቀርቡ የአፍሪካ አጀንዳዎች እንደሚቀረጹም የአፍሪካ ህብረት መረጃ ያመለክታል። ጉባኤው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ራዕዮች ወደ ሚጨበጥ ውጤት የመቀየር ስራን ጠንካራ የጋራ አቋም የሚያዝበት ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል። የኢትዮጵያ መንግስት እና የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን በጉባኤው ትርጉም ያለው ውጤት እና ለውጥ የሚፈጥር ውይይት እንዲካሄድ በጋራ እየሰሩ ይገኛሉ። በጉባኤው ላይ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች፣ አርሶ አደሮች፣ ተመራማሪዎች፣ የግሉ ዘርፍ፣ ዓለም አቀፍ አጋሮችና ሌሎች ተዋንያን እንደሚሳተፉ ተገልጿል።
በክልሎቹ በቀጣይ ሁለት ወራት መደበኛና ከመደበኛ በላይ የዝናብ ስርጭት ሊኖር ይችላል
Aug 18, 2025 113
ሀዋሳ፤ ነሀሴ 12/2017 (ኢዜአ)፡-በቀጣይ ሁለት ወራት በሲዳማ፣ ደቡብ ኢትዮጵያ፣ ማዕከላዊ ኢትዮጵያና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልሎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ የዝናብ ስርጭት ሊኖር እንደሚችል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢኒስቲትዩት አስታወቀ። ድንገተኛ ጎርፍና የመሬት መንሸራተት አደጋ ሊከሰት ስለሚችልም ተገቢውን ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባም ተመላክቷል። በኢኒስቲትዩቱ የሲዳማ፣ ደቡብ ኢትዮጵያ፣ ማዕከላዊ ኢትዮጵያና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልሎች መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ከፍያለው አየለ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በክልሎቹ እስከ መጪው ጥቅምት ወር ድረስ መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ ሊመዘገብ ይችላል። አብዛኛው የሲዳማ፣ ማዕከላዊ ኢትዮጵያና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልሎች እንዲሁም የደቡብ ኢትዮጵያ ደጋማ አካባቢዎች የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ መሆናቸውን አስታውሰዋል። የተቀሩት የደቡብ ኢትዮጵያ ቆላማ አካባቢዎች ደረቃማ ሆነው እንደሚቆዩ የጠቆሙት አቶ ከፍያለው፣ በእነዚህ ክልሎች የክረምቱ ዝናብ መደበኛና ከመደበኛ በላይ እንደሚሆንም ጠቁመዋል። በቀሩ የክረምት ወራት ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚጠበቅ የሚቲዎሮሎጂ ትንበያው ያሳያል ያሉት አቶ ከፍያለው፣ በዚህም በክልሉ ተዳፋታማ በሆኑ ቦታዎች፣ በወንዝ ዳር አካባቢዎችና በታችኛው የሐይቆች ተፋሰስ ድንገተኛ ጎርፍ እና በማሳ ላይ ውሃ መተኛት የሚጠበቁ ክስተቶች መሆናቸውን ተናግረዋል። የሲዳማ ክልል አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር አበራ ዊላ በበኩላቸው እንዳሉት የክረምት ዝናብን ተከትሎ የሚያጋጥሙ ክስተቶችን ለመከላከል ኮሚሽኑ ከኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ጋር ተቀራርቦ እየሰራ ይገኛል። በየጊዜው የሚቲዎሮሎጂ መረጃን መሰረት በማድረግ በክልሉ በአራት ዞኖች ካሉ 36 መዋቅሮች ጋር ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ ቢያጋጥም ጉዳት እንዳይደርስ ለመከላከል እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። አምና በክረምት ወቅት በነበረው ሀይለኛ ዝናብ በክልሉ ወንሾ ወረዳ የመሬት መንሸራተት አደጋ አጋጥሞ እንደነበር ያስታወሱት ኮሚሽነሩ፣ በዚህም የሰው ህይወት ከማለፉ ባለፈ በንብረት ላይ ጉዳት ደርሷል ብለዋል። ዘንድሮ መሰል ችግሮችን ቀድሞ ለመከላከል በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ኮሚሽነር አበራ ገልጸዋል። ህብረተሰቡ በክረምቱ እየጣለ ያለውን ዝናብ ተከትሎ ሊከሰት በሚችል ድንገተኛ የጎርፍ እና የመሬት መንሸራተት አደጋ ለችግር እንዳይጋለጥ ተገቢውን ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበትም አሳስቧል።
የተከልናቸው የፍራፍሬ ችግኞች ጸድቀው ለፍሬ እንዲበቁ እንክብካቤ እናደርጋለን
Aug 17, 2025 137
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 11/2017(ኢዜአ)፡- የተከልናቸው የፍራፍሬ ችግኞች ጸድቀው ለፍሬ እንዲበቁ ቀጣይነት ያለው እንክብካቤ እናደርጋለን ሲሉ የኢትዮጵያ ካፒታል ገበያ አስተዳደራዊ ፍርድ ቤት አመራርና ሠራተኞች አስታወቁ፡። የአስተዳደራዊ ፍርድ ቤቱ አመራርና ሠራተኞች ሸገር ከተማ መነ አቢቹ ክፍለ ከተማ ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር በመሆን የአፕል ችግኞችን በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል፡፡ የፍርድ ቤቱ ሰብሳቢ ዳኛ አብነት ዘርፉ እንደተናገሩት ኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሐግብር እያከናወነች ያለው ተግባር ለሌሎች የዓለም ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ነው፡፡ እየተተከሉ ያሉ ችግኞች የኢትዮጵያን የደን ሀብት ከማሳደግ በተጨማሪ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በሚሠራው ሥራ ትልቅ አስተዋፅኦ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ የካፒታል ገበያ አስተዳደር ፍርድ ቤት አመራርና ሠራተኞች አሻራቸውን ማሳረፋቸው የሚኮሩበት ተግባር መሆኑንም አክለዋል። በቀጣይ ችግኞችን ከመትከል ባለፈ የተተከሉ ችግኞች ፍሬ እንዲያፈሩ ከአካባቢው ነዋሪዎች ጋር እንደሚንከባከቡ ጠቁመዋል። ከቤተሰቧ ጋር በችግኝ ተከላው የተሳተፈችው የአስተዳደራዊ ፍርድ ቤቱ ሠራተኛ ገነት አዲሱ ችግኝ መትከል ለነገ ትውልድ ምቹ ሀገር መገንባት መሆኑን ተናግራለች፡፡ በዚህ መርሐግብር ልጆቿ መሳተፋቸው ነገ የአረንጓዴ አሻራ ጥቅምን በተጨባጭ ተረድተው በቀጣይ ተሳትፏቸውን እንዲያጠናክሩ ያስችላቸዋል ብላለች። ሌላኛው የተቋሙ ሠራተኛ ዳዊት ሙሉጌታ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር መሳተፍ ለትውልድ ትልቅ አሻራ ማሳረፍ በመሆኑ ኩራት እንደሚሰማው ገልጿል። የተስተካከለ የአየር ንብረት እንዲኖር ከማስቻል በተጨማሪ አካባቢ ውብ እንዲሆን ትልቅ ሚና ያለው በመሆኑ መሳተፋቸው ትልቅ ደስታ እንደፈጠረላቸው የተናገሩት ደግሞ የመና አቢቹ ነዋሪ መቅደስ አግደው ናቸው። የመነ አቢቹ ክፍለ ከተማ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ ገመቺስ ዳንኤል በዘንድሮ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ህብረተሰቡ፣ የመንግስት ተቋማትና ሌሎች በርካታ ችግኞችን መትከላቸውን ተናግረዋል። የተተከሉት ችግኞች ለፍሬ እንዲበቁ በማድረግ የአካባቢው ነዋሪ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ እንዲሆን የመንከባከብ እና የመጠበቅ ስራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል።
በጣና ሀይቅ ዙሪያ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት የሀይቁን ዘላቂ ደህንነት በጠበቀ መልኩ ሊሆን ይገባል
Aug 17, 2025 121
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 11/2017(ኢዜአ)፡- በጣና ሀይቅ ዙሪያ የሚከናወኑ የልማት ተግባራት የሀይቁን ዘላቂ ደህንነት በጠበቀ መልኩ ሊሆን እንደሚገባ ተመለከተ። የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃና ደን ባለስልጣን የጣና ኃይቅን ህልውና መጠበቅ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ከሆቴሎች፣ ድርጅቶች፣ የኃይማኖት ተቋማትና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በባህርዳር ከተማ መክሯል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአማራ ክልል ገጠር ዘርፍ አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ኃላፊ ድረስ ሳህሉ(ዶ/ር) በመድረኩ እንደገለጹት የክልሉም ሆነ የኢትዮጵያ ጌጥ የሆነውን የጣና ሃይቅ መጠበቅ የሁሉም አካላት ሃላፊነት ነው። በተለይም በሃይቁ ዙሪያና አቅራቢያ እንደ ሆቴል፣ ሪዞርትና ሌሎች የልማት ስራዎች የሚሰሩ አካላት ስራቸውን ሀላፊነት በተሞላበት መንገድ ማከናወን እንዳለባቸው አሳስበዋል። የፍሳሽ ቆሻሻ አወጋገድ ስርዓታቸውን በማዘመን፣ የሃይቁን ወሰን ባለመጋፋትና የሀይቁን ደህንነት በሚያረጋግጥ መልኩ ስራቸውን ማከናወን እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። በሀይቁ ዙሪያ የሚከናወኑ ልማቶች ህግና መመሪያን ባከበረ መልኩ መሆን እንዳለበትም መክረዋል። የአማራ ክልል አካባቢ ጥበቃና ደን ባለስልጣን ኃላፊ ተስፋሁን አለምነህ በበኩላቸው በጣና ሃይቅ ላይ ፍሳሽና ደረቅ ቆሻሻን በመልቀቅና ድንጋይ እየሞሉ በመደልደል የሀይቁን ህልውና የሚፈታተኑ አካላት ጥንቃቄ ማድረግ አለባቸው። ባለስልጣኑ በቀጣይ የሀይቁን ደህንነት የሚያስጠብቁ ህጎችንና መመሪያዎችን መሰረት በማድረግ ህጋዊ እርምጃ እንደሚወስድ አመላክተውል። የዛሬው ውይይትም እያንዳንዱ ባለድርሻ አካል የወጡ መመሪያዎችንና ደንቦችን በመገንዘብ ኃላፊነቱንና ግዴታውን አውቆ የልማት ስራዎችን እንዲያከናውን ግንዛቤ ለማስጨበጥ ነው ብለዋል። በመድረኩ ላይ የክልሉና ባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች፣ ባለሙያዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
አፍሪካውያን ለዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ፍትህ የሚጠይቁበት ጉባኤ
Aug 16, 2025 247
አፍሪካ የምንኖርባትን አለም ህልውና የሚያስጠብቅ እና የሚያስቀጥል ጠንካራ ኃይል ያላት አህጉር ናት ማለት ይቻላል። ከአማዞን ቀጥሎ ሁለተኛው የምድራችን ሳንባ እየተባለ የሚጠራው የኮንጎ ተፋሰስ በዚሁ አህጉር የሚገኝ ነው። ተፋሰሱ በርካታ ካርቦን ዳይኦክሳይድ አምቆ በመያዝ የአየር ንብረት ሚዛንን ይጠብቃል። እንደ አባይ፣ ኮንጎ እና ኒጀር የመሳሰሉ ወንዞች ከአፍሪካ ድንበር ተሻግረው በግብርና እና የስነ ምህዳር ጥበቃ ላይ እየተወጡት ያለው ሚና ትልቅ ነው። ከተንጣለለው የሳቫና የሳር መሬት እስከ ከርሰ ምድር የተፈጥሮ ጸጋዎች የአፍሪካ ብዝሃ ህይወት የዓለም ስነ ምህዳር በዘላቂነት እንዲቀጥሉ እያደረጉ ይገኛል። አፍሪካ ያላትን እምቅ የታዳሽ ኃይል ምንጭ በዓለም ንጹህ የኢነርጂ ኃይልን ለማስፋት ያለው ሚና ጉልህ መሆኑ አያጠራጥርም። አህጉሪቷ ዓለምን በተፈጥሯዊ ሀብቷ እየጠበቀች ቢሆንም እምብዛም ድርሻ በሌላት የአየር ንብረት ለውጥ ገፈት ቀማሽ ሆናለች። ተከታታይ ድርቅ እና ጎርፍ እንዲሁም የምግብ ዋስትና ማጣት ከቀውሶቹ መካከል ይጠቀሳሉ። የኢንዱስትሪ ዘመን አሃዱ ብሎ ከጀመረበት እ.አ.አ 1850ዎቹ አንስቶ ዓለም ላይ ከሚለቀቀው ካርቦን ዳይኦክሳይድ አፍሪካ ያላት ድርሻ ከ3 እስከ 4 በመቶ ብቻ መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። በአንጻሩ የበለጸጉ ሀገራት በዓለም ለይ በካይ ጋዝን በመልቀቅ 80 በመቶ የሚሆን ድርሻ አላቸው። እነዚህ የበለጸጉ ሀገሮች እ.አ.አ በ2009 በዴንማርክ ኮፐንሃገን 15ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ -15) ላይ በአየር ንብረት ለውጥ ተጎጂ ለሆኑ በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በየዓመቱ 100 ቢሊዮን ዶላር ለመስጠት ቃል ቢገቡም ቃል ኪዳናቸውን እየጠበቁ አይደለም። ለአፍሪካ አህጉር ጨምሮ ለሌሎች በማደግ ላይ ለሚገኙ ሀገራት ያደጉ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመከላከል ቃል የገቡትን 100 ቢሊዮን ዶላር እንዲያሟሉ ጥሪ እያቀረቡ ይገኛል። አየር ንብረት ለውጥ ፈተና ውስጥ ባለበት በአሁኑ ወቅት አፍሪካዊያንን ለዚህ አንገብጋቢ አጀንዳ በጋራ የሚያቆም ሁነት ከፊት ለፊታችን እየመጣ ነው። ኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ህብረት በጋራ የሚያዘጋጁት ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም በአህጉሪቷ መዲና አዲስ አበባ ይካሄዳል። ጉባኤው የአፍሪካ መሪዎች፣ አርሶ አደሮች፣ ተመራማሪዎች፣ ወጣቶች፣ ኢኖቬተሮች እና ለውጥ ፈጣሪዎች በአንድ ጥላ ስር የዘመኑ ትልቅ ፈተና በሆነው የአየር ንብረት ቀውስ እና መፍትሄው ላይ ይመክራሉ። ችግሩ አለ ብሎ ከማውራት ባለፈ እንደ አረንጓዴ አሻራ ያለ ሀገር በቀል የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄዎችም ይቀርባሉ። ጉባኤው የአፍሪካ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ላይ ፍትህ ሊሰጠን ይገባል የሚል ጠንካራ እና የጋራ ድምጽ የሚያሰሙበት ነው። አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የሚያስፈልጋትን ፋይናንስ የበለጸጉ ሀገራት እንዲሰጡም ጠንካራ ጥሪ ይቀርብበታል ተብሎ ይጠበቃል። 30ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ 30) በመጪው ህዳር ወር 2018 ዓ.ም በብራዚል ቤለም ከተማ ይካሄዳል። አፍሪካውያን በኮፕ 30 ላይ አህጉሪቷ ሊኖራት የሚገቡ አጀንዳዎችን እና የጋራ አቋሞችን ያዘጋጃሉ።በጉባኤው ከአዲስ አበባ የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄ ድምጽ ጎልቶ ይሰማል። ዓለም የሚቀርበውን ጥሪ ጆሮ ሰጥቶ በማዳመጥ በአየር ንብረት ለውጥ የተግባር ምላሽ እንደሚሰጥም ይጠበቃል።
ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ ያስመዘገበችው ስኬት የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባዔን እንድታስተናገድ አስችሏታል
Aug 15, 2025 169
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 9/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት የተመሰረተ የኢኮኖሚ ሥርዓት በመገንባት ያስመዘገበችው ስኬት ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባዔ ለማስተናገድ ተመራጭ እንዳደረጋት የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) ገለጹ። ኢትዮጵያ በአሥር ዓመት መሪ የልማት ዕቅዷ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ የኢኮኖሚ ልማት ለመገንባት የሚያስችሉ ሥራዎችን በማከናወን ላይ ትገኛለች። በዚህም በብዝኃ ኢኮኖሚ መርህ ለአካባቢ ደኅንነት መሰረት የሆነ ስኬታማ የታዳሽ ኃይልና የአረንጓዴ አሻራ የልማት መርሃ ግብሮች በመቅረጽ ሰፋፊ ውጤቶችን አስመዝግባለች። ለአብነትም የታላቁ ኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን ጨምሮ የፀሐይና የነፋስ ኃይል፣ የባዮ ጋዝ ፕሮጀክቶችና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የኢኮኖሚ ሥርዓት ግንባታ መገለጫዎች ናቸው። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የምትገነባው የኢኮኖሚ ሥርዓት የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን መቀነስ ላይ የተመሰረተ ነው። በታዳሽ ኃይል ላይ የተመሰረተ አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የምታደርገው ጥረትም የበካይ ጋዝ ልቀትን በመቀነስ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን መከላከል የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም ኢትዮጵያ በአረንጓዴ የኢኮኖሚ ሥርዓት ግንባታ እያስመዘገበች ያለው ስኬት ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባዔ ለማስተናገድ ተመራጭ እንዳደረጋት ተናግረዋል። ለአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ የማይበገር የኢኮኖሚ ሥርዓት ለመገንባት የሚደረገው ጥረትም የግብርና ምርታማነትን እያሳደገ እንደሚገኝ አብራርተዋል። የፓሪስ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስምምነትን መነሻ በማድረግ የተቀረጸው ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የልማት ስትራቴጂ የኢትዮጵያን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ሕብረት ጋር በመተባበር ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባዔ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ለማስተናገድ ከፍተኛ ዝግጅት እያደረገች ትገኛለች። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ "የዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሔዎችን ማፋጠንና የአፍሪካን የአረንጓዴ ልማት በገንዘብ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ ይካሄዳል።
ጣና ሐይቅን ከእምቦጭ መጤ አረም የመከላከል ተግባር ሕብረተሰቡን በማሳተፍ እየተከናወነ ነው - ባለስልጣኑ
Aug 15, 2025 120
ባሕር ዳር፤ ነሐሴ 9/2017(ኢዜአ)፡- ጣና ሐይቅን ከእምቦጭ መጤ አረምና ሌሎች ችግሮች የመከላከል ተግባር ሕብረተሰቡን በማሳተፍ እየተከናወነ እንደሚገኝ የክልሉ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። ጣና በውስጡ የተለያዩ የዓሣ ዝርያዎችን ጨምሮ ለቱሪዝም ዘርፉ ማደግ የጎላ ፋይዳ ያላቸው ገዳማትና ቅርሶች የሚገኙበት ሐይቅ መሆኑ ይታወቃል። በዚህም በዙሪያው ለሚኖሩ የአካባቢው ነዋሪዎች በዓሣ ማስገር ስራ፣ ቱሪስቶችን በጀልባ በማጓጓዝና በሌሎች ዘርፎች በመሰማራት ከፍተኛ የገቢ ምንጭ ሆኖ እያገለገለ ይገኛል። የክልሉ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ሃላፊ ተስፋሁን አለምነህ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ሐይቁ እምቦጭ አረምን ጨምሮ ሌሎች መጤ አረሞች፣ በደለል የመሞላት ስጋትና ከከተሞች ቆሻሻ ፍሳሽ የመለቀቅ አደጋ እያጋጠመው ነው። ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የአካባቢውን ማሕበረሰብ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ የአጭር፣ የመካከለኛ እና የረጅም ጊዜ እቅድ ተነድፎ የመከላከል ተግባር እየተከናወነ ይገኛል ነው ያሉት። በተለይም ለሐይቁ ስጋት የሆነውን የእምቦጭ አረም ለመከላከል ማህበረሰቡን በማስተባበርና ማሽኖችን በመጠቀም የማስወገድ ተግባር መቀጠሉን ተናግረዋል። በተያዘው በጀት ዓመት የሐይቁን አካል ከወረረው የእምቦጭ አረም ውስጥ የሰው ሃይልና ማሽን በመጠቀም 2ሺህ 600 ሄክታር ያህሉን ማስወገድ እንደተቻለ ጠቅሰዋል። አረሙን በማስወገድ ስራ ከ9 ሺህ በላይ የሰው ሃይል ማሳተፍ እንደተቻለ ጠቅሰው፤ አረሙ ካለው በፍጥነት የመራባት ባህሪ አንፃር አሁንም የሕብረተሰቡ ተሳትፎ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት አመልክተዋል። ሐይቁን በደለል ከመሞላት ስጋት በዘላቂነት ለመጠበቅ በዙሪያው እየተከናወነ ያለው የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን አብራርተዋል። ፍሳሽ ቆሻሻ ወደ ሐይቁ የሚለቁ ተቋማትንም በመለየት አስተዳደራዊ እርምጃ መወሰዱን አስታውሰው፤ የባሕር ሸሽ እርሻን ለማስቆም ሰፊ ጥረት እየተደረገ እንደሆነም አስረድተዋል። እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የሐይቁ ደህንነት በመጠበቅ ስጋት ከማይሆንበት ደረጃ እስከሚደርስ ድረስ ሕብረተሰቡን በማሳተፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አስታውቀዋል። ጣና ሐይቅ የኢኮኖሚና የቱሪዝም ምንጭ የሆነ ትልቅ የሀገር ሃብት በመሆኑ በአግባቡ ጠብቆ ለትውልድ ማስተላለፍ የግድ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለዚህም ሁሉም ሃላፊነቱን መወጣት እንደሚገባው አስገንዝበዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ኢትዮጵያ ከሌሎች ሀገራት ጋር ያላት የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን ለማጠናከር ጉልህ አስዋጽኦ እያበረከተ ነው
Aug 14, 2025 197
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 8/2017(ኢዜአ)፦ አረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ኢትዮጵያ ከሌሎች ሀገራት ጋር ያላት የህዝብ ለህዝብ እና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን ለማጠናከር ጉልህ አስዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሙና አህመድ ገለጹ። ሁለተኛው ዙር ዓለም አቀፍ "ፕላንት ፍራተርኒቲ" መርሃ ግብር የተጀመረ ሲሆን፤ ወደ ፓኪስታን አቅንቶ የኢትዮጵያን የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ተሞክሮ የሚያካፍለው የመጀመሪያው የወጣቶች ቡድን በዓድዋ ድል መታሰቢያ አሸኛኘት ተደርጎለታል። በመርሃ ግብሩ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ሙና አህመድ፣ የብልጽግና ፓርቲ ወጣቶች ክንፍ ፕሬዝዳንት አክሊሉ ታደሰ፣ በኢትዮጵያ የፓኪስታን አምባሳደር አቲፍ ሸሪፍ ሚያን እንዲሁም የክንፉ አመራር እና አባላት ተገኝተዋል። የወጣቶች ቡድኑ በፓኪስታን በሚኖረው ቆይታ የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር የሚያከናውን ሲሆን፤ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን የሚያጠናክሩ ተግባራት ላይ ትኩረት ያደረጉ ስራዎችን እንደሚያከናውንም ተገልጿል። ሚኒስትር ዴኤታዋ በመድረኩ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ዐሻራ ኢንሼቲቭ ያላትን ተሞክሮ ሌሎች ሀገራት ማካፈል መጀመሯ ዲፕሎማሲውን ከማጠናከር ባሻገር ለየህዝብ ለህዝብ ግንኙነቱ መጠናከር ጉልህ አስዋጽኦ እያበረከተ ነው። ወደ ፓኪስታን የሚያቀናው የወጣቶች ቡድንም ከችግኝ ተከላ ባለፈ የኢትዮጵያን ገጽታ በመገንባት፣ የውጭ ኢንቨስትመንት ፍሰት እንዲጨምር የማድረግ ድርብ ሃላፊነት እንዳለበትም ጠቁመዋል። በፓኪስታን ቆይታችሁ የሁለቱን ሀገራት ግንኙነትን የሚያጠናክሩ ተግባራት ላይ ትኩረት በማድረግ ልትሰሩ ይገባል ሲሉም ተናግረዋል። የብልጽግና ፓርቲ ወጣቶች ክንፍ ፕሬዝዳንት አክሊሉ ታደሰ በበኩላቸው፤ በመጀመሪያው ዙር "ፕላንት ፍራተርኒቲ" መርሃ ግብር በስምንት የአፍሪካ ከተሞች ወጣቶች የኢትዮጵያን ተሞክሮ በማካፈል ውጤታማ ስራ ማከናወናቸውን ገልጸዋል። ዛሬ በይፋ በተጀመረው ሁለተኛው ዙር መርሃ ግብር በተመሳሳይ ወጣቶች በስምንት የአፍሪካና ከአፍሪካ ውጭ ባሉ ሀገራት የአረንጓዴ ኢኒሼቲቭ ተሞክሮን እንደሚያካፍሉ አብራርተዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት የተቀረጸው አረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ ሌላው ገጸ በረከት መሆኑን በመግለጽ። በኢትዮጵያ የፓኪስታን አምባሳደር አቲፍ ሸሪፍ ሚያን እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ እና ፓኪስታን በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ ተመሳሳይ ፈተናዎች የሚጋሩ በመሆናቸው በዚህ ላይ በጋራ መስራታቸው ውጤታማ ያደርጋቸዋል ነው ያሉት። ፓኪስታን ከኢትዮጵያ አረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቭ የምትቀስማቸው በርካታ ተሞክሮዎች መኖራቸውንም ተናግረዋል። የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋም ግብርና ዙሪያ ፓኪስታን ልምድ ያላት መሆኑን ገልጸው፤ ይሄንን ልምድ ለኢትዮጵያ ለማካፈል ዝግጁ ናት ብለዋል።
ከጉርስ እስከ ውርስ የሚዘልቅ ሃብት
Aug 14, 2025 206
(በሳሙኤል አየነው - አርባምንጭ)-ከጉርስ እስከ ውርስ የሚዘልቅ ሃብት... በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ምዕራፍ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር "በአንድ ሰው 40 ችግኝ" በሚል መሪ ሃሳብ በ2011 ዓ.ም ነበር የተጀመረው። በዚሁ መርሃ ግብር ከ4 ነጥብ 7 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ኢትዮጵያዊያን አሻራቸውን የማኖር ጥረታቸውን ቀጠሉ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነት በተጀመረው የአረንጓዴ ኢንሸቲቭ የተራቆቱ አካባቢዎች ከማገገማቸው ባለፈ የምግብ ሉአላዊነትን የማረጋገጥን ድርብ አላማ ሰንቆ ለተከታታይ ሰባት አመታት ዘልቋል። ኢትዮጵያዊያን በዘንድሮው መርሃ ግብር "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መርህ በአንድ ጀምበር ብቻ 714 ነጥብ 7 ሚሊዮን ችግኞችን በመትከል ምንም ነገር ማሳካት እንደሚችሉ በተግባር ያሳዩበት ታሪካዊ አጋጣሚ ሆኗል። ባለፉት አመታት የተተከሉ ችግኞች ውጤትና የዘንድሮውን ተሳትፎ የኢዜአ ሪፖርተር በአርባ ምንጭ እና አካባቢው ነዋሪዎችን አነጋግሯል። የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪ አቶ ተዘራ ቀፃዮ፤የአረንጓዴ አሻራ የተቆረጡ ዛፎችን በመተካት የተራቆቱ አካባቢዎችን ማልበስ ያስቻለና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እድል ፈጥሯል ብለዋል። የዚህ ስኬት ሚስጢሩ በተባበረ ክንድ መስራትና ለቁም ነገር ማብቃት በመቻላችን ነው ሲሉም አስረድተዋል። ሁሉን ከዳር ዳር ያነቃቃው ይህ ሀገራዊ ፕሮጀክት ተከታታይነት ያለው ሰፊ አሻራ እንድናኖር ያደረገ ነው ያሉት አቶ ተዘራ አሻራችንን እያኖርን፣ ከተፈጥሮ ጋር እየታረቅን እያለማንና እየተጠቀምን ከጉርስ እስከ ውርስ የሚዘልቅ ሃብት እየፈጠርን እንገኛለን ብለዋል። በምድረ ገነትነት የምትታወቀው አርባምንጭ እና አካባቢው ባለፉት ዓመታት የአረንጓዴ ካባ እየለበሰ ይበልጥ ውብ እና ማራኪ እየሆነ መምጣቱንም አንስተዋል። ለአርባ ምንጭና አካባቢው ነዋሪዎች ችግኝ መትከልና መንከባከብ ልምድ እየሆነ መምጣቱን የተናገሩት አቶ ተዘራ ለመጪው ትውልድ ምቹ አካባቢን የመፍጠር ስራ በተጠናከረ መልኩ ቀጥሏል ብለዋል። በአርባምንጭ ከተማ የ"ነህሚያ" እንስሳት እርባታና ማድለብ ማህበር ሰብሳቢ ወጣት ህዝቅኤል ኦሎባ፤ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተፈጥሮን ከመጠበቅም ባለፈ ከድህነት የመውጫ ሁነኛ መፍትሄ እየሆነ መጥቷል ብሏል። የአረንጓዴ አሻራ ልማት በአንድ በኩል ለደን ጥበቃና እንክብካቤ በሌላ በኩል ለእንስሳት መኖ እየዋለ ሲሆን በፍራፍሬ ልማትም የምግብ ዋስትና መሰረት እያኖረ መሆኑን አንስቷል። የኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ ልማት ከኢትዮጵያም ባለፈ ከጎረቤት አገራት ጋር የጋራ ልማትና ተጠቃሚነትን እያረጋገጠ ያለ ስለመሆኑም አስረድቷል። በመሆኑም አሻራችንን በማኖር ሀገርን ማልማት፤ ለነገ የሚሆን ጥሪት ማኖርና የትውልዶች ውርስ እንዲሆን የሁላችንም ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል ብሏል። በክልሉ ርእሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ሃሳብ አመንጭነት በ12 ዞኖች የአንድ ተራራ ልማት ኢኒሸቲቭ ተግባራዊ እየተደረገ ሲሆን በዚህም የከተማው ራስጌ ላይ የሚገኘው የጋንታ ተራራ ልማት ለአብነት የሚጠቀስ ሆኗል። በቅርቡ በዚሁ ተራራ ላይ አሻራቸውን ያኖሩት የብልጽግና ፓርቲ የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ሃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)፤ የአርባዎቹ ምንጮች ቤትና የእምቅ ተፈጥሮ ሃብቶች ባለቤት የሆነው አርባ ምንጭ ይበልጥ እያማረበትና እየተዋበ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የታዳሽ ሃይል እና የአረንጓዴ አሻራ ልማት የሰውን ልጅ ከተፈጥሮ ጋር የሚያስታርቅ፣ ሀገርን የማልማትና የምግብ ዋስትና መሰረት መሆኑን ተናግረዋል። ከመጪው ትውልድ የተበደርነውን የተፈጥሮ ሀብት በመጠበቅ ለቀጣዩ ትውልድ ምቹ ሀገር የማስረከብ ታሪካዊ ሃላፊነት አለብን ሲሉም አስገንዝበዋል። የአረንጓዴ አሻራ ልማት፣ የህዳሴ ግድብ ስኬት፣ በግብርና፣ ቱሪዝም፣ ኢንዱስትሪ እና አይ ሲቲ ጭምር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የጋራ ትርክት መገለጫዎችና ለኢትዮጵያ ብልጽግና ተስፋ የተሰነቅንባቸው መሆኑን ተናግረዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደን፣አከባቢጥበቃና ልማት ቢሮ ሃላፊ ግዛቴ ግጄ፤ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ የመገንባት ራዕይ መሳካት በክልሉ ተጨባጭ ማሳያዎች መኖራቸውን አንስተዋል። የአረንጓዴ አሻራ ለአትክልትና ፍራፍሬ ልማት እንዲሁም ለሌማት ትሩፋት የላቀ ትርጉም እንዳለው አንስተው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በመሆኑም ችግኞችን መትከል ብቻ ሳይሆን ጥበቃና እንክብካቤ በማድረግ ተፈጥሮን ማልማትና የምግብ ዋስትና መሰረት ማኖር ይገባል ብለዋል። በክልሉ በ12 ዞኖች በመንግስት፣ በግለሰብ፣ በማህበራትና መንግስታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች 1 ሺህ 495 ችግኝ ጣቢያዎች መኖራቸውን ጠቅሰው በእነዚህም ለምግብነትና ሌሎችም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማፍላት ስራ በመከናወን ላይ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ በመትከል የማንሰራራት ዓላማ በመሰነቅ ለአረንጓዴ ልማት ስኬት እየተጋን እንገኛለን ብለዋል።
የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የግሉ ዘርፍ ንቁ ተሳትፎ ሊያደርግ ይገባል-ፕላንና ልማት ሚኒስቴር
Aug 14, 2025 126
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 8/2017(ኢዜአ)፦የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት የግሉ ዘርፍ ንቁ ተሳትፎ ሊያደርግ እንደሚገባ የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ህብረት ጋር በመተባበር ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም እንደምታስተናግድ ይታወቃል። ጉባኤው "ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፥ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ ይካሄዳል። የፕላን እና ልማት ሚኒስቴር ጉባኤውን በተመለከተ ከግሉ ዘርፍ እና የፋይናንስ ተቋማት አመራሮች ጋር በአዲስ አበባ እየተወያየ ነው። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት እንዳሉት ለሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ ሰፊ ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል። ጉባኤው ለሰው ልጆች ፈተና የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል እና ለመቋቋም የሚያስችሉ ውሳኔዎች የሚተላለፉበት ትልቅ ጉባኤ መሆኑን ገልጸዋል። ጉባኤው የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን ለመቅረፍ በርካታ የመፍትሄ ሀሳቦች የሚቀርቡበት እንዲሁም ለአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄ የሚሆኑ አህጉራዊ አቅሞች የሚፈጠሩበት መሆኑን ገልጸዋል። እንደ ሚኒስትር ዴኤታው ገለጻ በጉባኤው በአጀንዳነት ከተያዙ ጉዳዮች መካከል የአየር ንብረት ለውጥ በግሉ ዘርፍ ላይ እያሳደረ ያለው ተጽእኖ አንዱ ነው። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የሚያስችሉ ተጨባጭ ስራ እየሰራች መሆኑን ገልጸዋል። በጉባኤው የኢትዮጵያ ምርጥ ተሞክሮዎች እንደሚቀርቡ ጠቁመው፥ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት ውስጥ የግሉ ዘርፍ ንቁ ተሳትፎ ማድረግ እንዳለበት አመላክተዋል። የግሉ ዘርፍ ተዋንያን በሙያ፣ በገንዘብ እንዲሁም በሀሳብ በማገዝ በጉባኤው አዎንታዊ ሚና መጫወት እንዳለባቸው ጠቁመዋል። ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ አፍሪካውያን ድምጻቸውን ከማሰማት ባሻገር ለአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄ በግንባር ቀደምነት እየሰሩ መሆኑን ለዓለም የሚያሳዩበት መድረክ እንደሚሆን ይጠበቃል።
የህዳሴ ግድብ የሚገኝበት አካባቢ የሚተከሉ ችግኞች የግድቡን ህልውና የሚጠብቁ ናቸው
Aug 14, 2025 149
አሶሳ፤ ነሐሴ 08/2017 (ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የሚገኝበት አካባቢ የሚተከሉ ችግኞች የግድቡን ህልውና የሚጠብቁ ናቸው ሲሉ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤሊያስ ተናገሩ። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ምርታማነትን በማሳደግ እንደ ሀገር ከተረጂነት ለመውጣት ለሚደረገው ጥረት ከፍተኛ እገዛ እንዳለውም ተገልጿል። የፌዴራል ተቋማት አመራሮችና የየክልሉ ነዋሪዎች በክረምቱ ወራት ሰፋፊ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በማካሄድ ላይ ይገኛሉ። ታላቁ የህዳሴ ግድብ የሚገኝበት የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልም የተለያዩ ወረዳዎች የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብሩ ተጠናክሮ ቀጥሏል። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የፌዴራል ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ሃላፊዎች ግድቡ የሚገኝበት አካባቢ የሚተከሉ ችግኞች በተለይም የግድቡን ህልውና ዘላቂ የሚያደርጉ መሆናቸውን አንስተዋል። የግብርና ሚኒስቴር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤሊያስ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በመትከሉ ረገድ በህብረተሰቡ ተሳትፎ ከዕቅድ በላይ መከናወኑን ገልጸዋል። በተለይም አገሪቷ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለምታደርገው ግስጋሴ ፈተና የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥ ለመቋቋም የአረንጓዴ አሻራን አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባ ጠቁመዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአየር ንብረት ለውጥን ተከትሎ ለሚመጡ ጫናዎች ተጨባጭ ምላሽ የሚሰጥ እርምጃ መሆኑን አንስተዋል። ለዚህም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እየተተከሉ መሆኑን አንስተው፤ በተለይም የህዳሴ ግድብ የሚገኝበት አካበቢ የሚተከሉ ችግኞች ግድቡ በደለል እንዳይሞላ በማድረግ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጸዋል። ሚኒስቴሩ ከተጠሪ ተቋማት ጋር በመሆን ከ200 ሺህ በላይ ችግኞችን በመትከል ሀገራዊ ሀላፊነቱን እየተወጣ መሆኑንም አንስተዋል። በመጪው ጳጉሜ ወር ላይ የሚካሄደው የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ኢትዮጵያ ለአረንጓዴ አሻራ የሰጠችውን ትኩረት በተጨባጭ የምታሳይበት እንደሆነም አብራርተዋል። ጉባኤው በኢትዮጵያ እንዲካሄድ መወሰኑ ለአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠት አገሪቷ እያከናወነችው ያለውን ተሞክሮ በተለያዩ ሀገራት ለማስፋፋት ዕድል የሚፈጥር እንደሆነም ገልጸዋል። የግብርና ሚኒስቴር ከተጠሪ ተቋማት ጋር በመተባበር በክልሉ የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት ተግባራትና የችግኝ ተከላ መርሃግብር ማከናወናቸው ይታወሳል ። በመርሃግብሩ ላይ የሚኒስቴሩ እና ተጠሪ ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች፣ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጌታሁን አብዲሳ እና የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።
በሚዛን አማን ከተማ የተራቆተ አካባቢን አረንጓዴ በማልበስ ለቁንዶ በርበሬ ልማት እየዋለ ነው
Aug 13, 2025 132
ሚዛን አማን ፤ ነሐሴ 7/2017 (ኢዜአ)፡- በሚዛን አማን ከተማ የተራቆተ አካባቢን አረንጓዴ በማልበስ ለቁንዶ በርበሬ ልማት እየዋለ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ። በከተማዋ የአረንጓዴ አሻራ ልማት በአርሶ አደሮች ጓሮ፣ በተቋማት ግቢ እና በመንግስት የወል መሬቶች ላይ ላለፉት ስድስት ዓመታት ሲከናወን ቆይቷል። ከተማ አስተዳደሩ በሚዛን አማን ከተማ ካሉ የወል መሬቶች መካከል የድንጋይ ማዕድን የሚመረትበት የአማን ቀበሌን ከ2014 ዓ.ም ጀምሮ በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር አረንጓዴ የማልበስ ስራ ሲያከናውን ቆይቷል። የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ ኢንጂነር ሰሎሞን ሌዊ የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሀግብር የተራቆቱ አካባቢዎች መልሰው እንዲያገግሙ ከማድረግ ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን በኩታገጠም ለማልማት ማስቻሉን ተናግረዋል። ለአብነትም ቀደም ሲል ለከተማዋ የልማት ሥራ ድንጋይ ለማውጣት በሚደረግ ቁፋሮ ከጥቅም ውጭ ሆኖ የነበረው በአማን ቀበሌ የጋቡቃ መንደርን በአረንጓዴ አሻራ መልሶ በማልማት ቁንዶ በርበሬ መተከሉን ጠቅሰዋል። ይህም አካባቢውን አረንጓዴ ከማልበስ ባለፈ ከቁንዶ በርበሬ ልማት ህብረተሰቡ የኢኮኖሚ ተጠቃሚ እንዲሆን ለማድረግ አስችሏል ብለዋል። የተራቆቱ ቦታዎች በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ችግኝ ከመትከል ባለፈ ከሰውና ከእንስሳት ንኪኪ ነጻ መደረጋቸው ውጤት አስገኝቷል ያሉት ደግሞ የከተማ አስተዳደሩ ግብርና፣ አካባቢ ጥበቃና ኅብረት ሥራ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ምስራቅ አስናቀ ናቸው። የአረንጓዴ ልማት ሥራውን በማጠናከር ለቁንዶ በርበሬ ቅመም ድጋፍ እንዲሆን የግራቪሊያ ዛፎች አብረው እንዲተከሉ መደረጋቸውን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት ከተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ሥራዎች ልምድ በመውስድ በተራቆቱ አካባቢዎች ችግኝ እየተከሉ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የከተማዋ ነዋሪ አቶ ትዕዛዙ ኬንጫ ናቸው። የተተከሉ ችግኞች ጸድቀው ለሚፈለገው ዓላማ እንዲውሉ ተገቢ እንክብካቤ እንደሚያደርጉም ተናግረዋል። በአረንጓዴ አሻራ ልማት የተራቆቱ ቦታዎች መልሰው ማገገማቸው የሕብረተሰቡን ችግኝ የመትከል ተነሳሽነት እንዳሳደገው የገለጸው ደግሞ ሌላው የከተማዋ ነዋሪ ወጣት ተዘራ ጥላሁን ነው። ችግኞችን ከመትከል ባሻገር መንከባከብ ያለውን ውጤት በከተማው ጋቡቃ አካባቢ የተተከለው የግራቪላ ዛፍ ማሳያ መሆኑን ጠቅስዋል። በሚዛን አማን ከተማ በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ፍራፍሬን ጨምሮ የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በስፋት እየተተከሉ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።
ከክረምቱ ጋር ተያይዞ ሊያጋጥም የሚችለውን የጎርፍ አደጋ የመከላከሉ ተግባር ተጠናክሮ እንደቀጠለ ነው
Aug 13, 2025 118
ጅግጅጋ፣ ነሐሴ 7/2017 (ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል ከክረምቱ ወራት ጋር ተያይዞ ሊያጋጥም የሚችለውን የጎርፍ አደጋ አስቀድሞ ለመከላከል የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን የክልሉ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ገለጸ። በክረምት ወራት ከወንዞች መሙላትና ተዳፋታማ የሆነ የመሬት አቀማመጥ ባላቸው አካባቢዎች ደግሞ ደራሽ የጎርፍ አደጋ ይከሰታል። ይኸንኑ ስጋት ከግምት በማስገባት የዋቤና ገናሌ ወንዞች አቋርጠው የሚፈሱበት የሶማሌ ክልል ሊያጋጥም የሚችለውን አደጋ ስጋት ለመከላከል የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ስራዎች ሲሰሩ መቆየታቸው ተገልጿል። የክልሉ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን የቅድመ ማስጠንቀቂያ እና ምላሽ አስተዳደር አስተባባሪ አቶ አብዲቃድር ሙሁመድ ለኢዜአ እንደገለጹት በክረምቱ ወቅት ሊያጋጥም የሚችል የጎርፍ አደጋዎችን አስቀድሞ ለመከላከል የሚያስችሉ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል። በዚህም ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ የሆኑ ነዋሪዎችን ወደ ተሻለ ቦታ የማስፈርና አደጋ እንዳለባቸው የተለዩ አካባቢዎች ላይ ደግሞ የቅድመ ጥንቃቄ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል። በበጋው ወራት የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የዚሁ ጥረት አካል መሆናቸውን ያነሱት አስተባባሪው የለሙ ተፋሰሶችን ደግሞ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በችግኝ የመሸፈን ሥራዎችም እየተሰሩ ነው ብለዋል። በተለይም የተጎዱ መሬቶች ላይ ችግኝ መትከል ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸው፤ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በቋሚነት መሰራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአካባቢ ጥበቃ ስራ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥና የህብረተሰቡን የስነ-ምግብ ስርዓት ማሻሻል ላይ ጉልህ ድርሻ እንዳለው ገልጸው፤ በዚህ ረገድ ውሃ በመያዝ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ ላይ በሰፊው እየተሰራ ነው ብለዋል። በተያዘው ክረምትም በሚጥለው ዝናብ የሚከሰተውን የጎርፍ ስጋት በመከላከል ላይ ህብረተሰቡም የሚተላለፉ የጥንቃቄ መልዕክቶችን በአግባቡ በመተግበር ራሱን መጠበቅ እንዳለበትም አቶ አብዲቃዲር አሳስበዋል። ከዚሁ ጋር ተያይዞም ሊከሰቱ የሚችሉ በሽታዎችን ለመከላከል ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት የቅድመ ጥንቃቄ ሥራዎች መሰራታቸውን ገልጸዋል። ኮሚሽኑ ከኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢኒስቲትዩት ጋር በመተባበር መረጃዎችን ለህብረተሰቡ የሚሰጡ የቅድመ ማስጠንቀቂያ መልእክቶች እንደሚያስተላልፍ ገልጸው፤ መልዕክቶቹን በመከታተል የቅድመ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚያስፈልግም አሳስበዋል።
በአፋር ክልል በመካከለኛውና ታችኛው አዋሽ የውሃ ሙላት የስጋት ቀጣናዎች የቅድመ ጥንቃቄ ስራ ተከናውኗል
Aug 12, 2025 234
ሠመራ፣ ነሐሴ 6/2017(ኢዜአ) ፡-በአፋር ክልል በመካከለኛውና ታችኛው አዋሽ የውሃ ሙላት የስጋት ቀጣናዎች የቅድመ ጥንቃቄ ስራዎች መከናወናቸውን የክልሉ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን አስታወቀ። በአዋሽ ተፋሰስና በአንዳንድ የሀገሪቱ አካባቢዎች ቅጽበታዊ ጎርፍና የወንዝ ውሃ ሙላት የመከሰት ሁኔታ እንዳለ ይታወቃል። ይኸንኑ ስጋት ከግምት በማስገባት የአዋሽ ወንዘ ተፋሰሶችን የጎርፍ አደጋ ስጋት ለመከላከል የሚያስችል ከተለያዩ ሴክተር መስሪያ ቤቶች የተውጣጣ ልዩ ግብረ ሃይል ተቋቁሞ ሲሰራ መቆየቱ ይታወሳል። ግብረ ሃይሉም በአካባቢው የጎርፍ አደጋ ቢከሰት አስቀድሞ ጥንቃቄ ለማድረግ፣ አስፈላጊውን ምላሽ ለመስጠትና የመልሶ ማቋቋም ስራ ለማከናወን የሚያስችል ነው። በዚሁ ጉዳይ ላይ ለኢዜአ ማብራሪያ የሰጡት የአፋር ክልል አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽነር መሐመድ ሁሴን፤ በመካከለኛውና ታችኛው አዋሽ የጎርፍ አደጋ ስጋት ያለባቸው ቀጣናዎች ተለይተው የቅድመ ጥንቃቄ ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። የአዋሽ ወንዝ ከዚህ ቀደም ያደርስ የነበረውን ጉዳት ከግንዛቤ በማስገባት አደጋው ከመከሰቱ በፊት የጥንቃቄ ሥራ፤ ቢከሰትም መከላከል የሚያስችል ዝግጁነት ስለመኖሩ አረጋግጠዋል። ይህንንም ለማከናወን በስፍራዎቹ ሁለት ጀልባዎች ዝግጁ መሆናቸውን ጠቅሰው የምግብ፣ የውሃ፣ የመጠለያና የመድሃኒት እንዲሁም በቤት ቁሳቁሶች ከመንግስትና ከተለያዩ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ጋር በመተባበር የቅድመ ዝግጅት ስራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል። በዚህ ወቅት ለሚነሱ አደጋዎች የሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን የክልሉ መንግስት የመጠባበቂያ በጀት የያዘ መሆኑን ጠቅሰው አቅምን ባማከለ መልኩ አስፈላጊ ዝግጅት መደረጉን አስታውቀዋል። ለአደጋ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ላይ የሚኖሩት የማህበረሰብ ክፍሎችም ባገኙት የጥንቃቄ መረጃዎች ከአካባቢው አስተዳደሮች ጋር በመተባበር የጥንቃቄ ሥራ መስራት እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል። የሐይማኖት አባቶች፣ የጎሳ መሪዎችና በየደረጃው ያሉ የአመራር አካላትም በእነዚህ የስራ ክንውኖች ወቅት የበኩላቸውን አስተዋፅኦ እንዲያበረክቱ ጥሪ አቅርበዋል። በአፋር ክልል ለጎርፍ አደጋ የስጋት አካባቢ ተብለው በ13 ወረዳዎች ውስጥ 62 ቀበሌዎች የተለዩ መሆኑም ታውቋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመከላከል የታዳሽ ኃይል ልማትን እያስፋፋች ነው - የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር
Aug 12, 2025 130
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 6/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመከላከል የታዳሽ ኃይል ልማትን እያስፋፋች እንደምትገኝ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) ገለጹ። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ አስመልክቶ ቅድመ ጉባኤ ኤግዚቢሽን እያካሄደ ይገኛል። ኤግዚቢሽኑ የኢነርጂ ሽግግር ጉዞ ለኢትዮጵያ እንዲሁም ለአፍሪካ የማይበገር እና ዝቅተኛ የካርቦን ልቀትን መሰረት ያደረገ ታዳሽ ኃይል ለመገንባት በዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ የጋራ ሥራዎችን ለማሳየት ያለመ ነው ተብሏል። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር ዴኤታ ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ (ዶ/ር) በኤግዚቢሽን መክፈቻው ላይ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን ተፅዕኖ ለመከላከል እና ለመቀነስ የተለያዩ ኢንሼቲቮችን በመንደፍ ተግባራዊ እያደረገች ትገኛለች። ለአብነትም የማይበገር የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ በመንደፍ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር እያከናወነች ያለችውን ሥኬታማ ስራ አንስተዋል። ይህም ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን ተፅዕኖ ለመከላከል እና ለመቀነስ ያላትን ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል። እንዲሁም የታዳሽ ኃይል ልማትን በማስፋት ተፅዕኖን ለመከላከል እና ለመቀነስ ትኩረት መስጠቷን ገልጸው፥ ይህም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ አረንጓዴ ዐሻራ ለሌሎች ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ዘመን ተሻጋሪ የልማት አጀንዳ ነው
Aug 9, 2025 177
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 3/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ምሳሌ የሚሆን ዘመን ተሻጋሪ የልማት አጀንዳ መሆኑን የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሰራተኞች ማህበር አባላት ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ከአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን የሰራተኞች ማህበር አባላት ጋር በመሆን የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር አካሂዷል። የችግኝ ተከላው በአዲስ አበባ የካ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ቤላ 18 ማዞሪያ ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ነው የተከናወነው። የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን የሰራተኞች ማህበር ፕሬዝዳንት ኑሁ ቺያም እንዳሉት፤ የአየር ንብረት ለውጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ነው። በአየር ንብረት ለውጥ ሳቢያ የሚመጡ ችግሮችን በዘላቂነት ለመከላከል ችግኞችን መትከል ሁነኛ መንገድ ነው ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ አረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ያመጣቸው ውጤቶች በአርዓያነት የሚጠቀሱ ናቸው ብለዋል። አዲስ አበባ አረንጓዴ እና ጽዱ ከተማ መሆኗን አድንቀው፥ ይህም ሌሎች ሀገራትን የበለጠ እንደሚያነሳሳ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ መንግሥት ህዝብን በስፋት በማነቃነቅ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ላይ እንዲሳተፉ ማድረጉ የሚደነቅና ለሌሎች ሀገራትም አብነት የሚሆን ነው ሲሉ ተናግረዋል። የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን የሰራተኞች ማህበር አባል ወጣት ጆን ማጎክ በበኩሉ፤ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ መሳተፉን ገልጾ ልዩ የደስታ ስሜት እንደፈጠረበት ጠቁሟል። አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የተያዙ ግቦች እንዲሳኩ ቁርጠኛ መሆኗን የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ ውጤት ዋነኛ ማሳያ መሆኑንም ተናግሯል። ሌላዋ የማህበሩ አባል ሞሮሲ ፑትሶዋ በበኩላቸው አረንጓዴ ዐሻራ በአህጉር ደረጃ በምግብ ራስን ለመቻል ለሚደረገው ጥረት አዎንታዊ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ የዳበረ የአረንጓዴ ዐሻራ ልምድ ያላት ሀገር መሆኗን በማንሳት፥ የአፍሪካ ሀገራት ውጤታማ የኢትዮጵያን ተሞክሮዎች በሀገራቸው በመተግበር ለትውልድ የሚተላለፍ ዐሻራን ማኖር እንዳለባቸው አመልክተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኅብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽነር አቶ ይመር ከበደ በበኩላቸው፤ የዛሬው ችግኝ ተከላ ኢትዮጵያ ለጉዳዩ የሰጠችውን ትኩረት በተጨባጭ ለማሳየት ዕድል የሚፈጥር ነው ብለዋል። ይህም የኢትዮጵያን ገጽታ በመገንባት በኩል ሚናው የላቀ መሆኑንም አስረድተዋል። የኢትዮጵያ አረንጓዴ ዐሻራ በአህጉር ደረጃ አጀንዳ እንዲሆን የተጀመረው ጥረት ግቡን እንዲመታ በማድረግ ረገድ የዛሬው መርኃ ግብር ከፍ ያለ አበርክቶ እንደሚኖረውም አብራርተዋል።
ደብረ ማርቆስ ከተማን ለነዋሪዎችና ለጎብኚዎች ምቹና ተመራጭ ለማድረግ እየተሰራ ነው
Aug 8, 2025 150
ደብረ ማርቆስ፤ ነሀሴ 2/2017(ኢዜአ)፡-የደብረ ማርቆስ ከተማን ጽዳትና ውበት በማጠናከር ለነዋሪዎችና ለጎብኚዎች ምቹና ተመራጭ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ። በደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር "የጽዱ ኢትዮጵያ" መርሃ ግብር አካል የሆነ የጽዳት ዘመቻ ዛሬ ተጀምሯል። የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ተሾመ ዋለ የጽዳት ዘመቻውን ሲያስጀምሩ እንደገለጹት፣ የሰላምና ጽዳት ሥራዎች ለሰው ልጅ ህይወት ወሳኝ በመሆናቸው በከተማዋ በትኩረት ይተገበራሉ። የጽዱ ኢትዮጵያን መርህ በከተማዋ በመተግበር ጽዳትን ከራስ ጀምሮ በቤተሰብ፣ በማህበረሰብና በአካባቢ ለማስፋት የሚያስችል ዘመቻ ዛሬ መጀመሩንም ተናግረዋል። የጽዳት ሥራውን አጠናክሮ በማስቀጠል ከተማዋን ጽዳትና ውበት በማጠናከር ለነዋሪዎችና ለጎብኚዎች ተመራጭ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። የከተማ አስተዳደሩ አካባቢ ጥበቃ፣ ጽዳትና ውበት ማስተባበሪያ ተጠሪ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ቸርነት አለማየሁ በበኩላቸው እንዳሉት፣ የከተማዋን ጽዳት በመጠበቅ ጤናማና አምራች ዜጋ ለመፍጠር ግብ ተይዞ እየተሰራ ነው። የጽዳት ሥራው ማህበረሰቡ ግቢውንና አካባቢውን ማጽዳት ባህሉ እንዲያደርግ ያለመ መሆኑን ገልጸው፣ "በከተማዋ የጽዱ ኢትዮጵያ" መርህን ለማሳካት ህብረተሰቡን በማሳተፍ ቀጣይነት ያለው ሥራ ይሰራል ብለዋል። የከተማዋን ውበት የሚያሳድጉ መሰረተ ልማቶች ላይ ቆሻሻ የሚጥሉ አካላት እንዳሉ የገለጹት አቶ ቸርነት፣ በጽዱ ኢትዮጵያ መርሀግብር ዛሬ የተጀመረው የጽዳት ዘመቻ ይሄን ችግር ይፈታል ብለዋል። ከጽዳት ዘመቻው ተሳታፊዎች መካከል ወጣት ትግስት ምህረት "የጸዳች ሀገርና ከተማ እንድትኖረን አካባቢዬን በማጽዳት የማደርገውን አስተዋጾ አጠናክራለሁ" ብላለች። የጽዱ ኢትዮጵያን መርህ መነሻ በማድረግ ዛሬ በተካሄደ የጽዳት ዘመቻ በከተማ አስተዳደሩ ያሉ የመንግስት ሠራተኞችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎችም ተሳትፈዋል።
አረንጓዴ አሻራ ለትውልድ ምቹ ሀገርን የመገንባት ትልቅ ተነሳሽነት ነው- የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች
Aug 8, 2025 157
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 2/2017(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ ለትውልድ ምቹ ሀገርን የመገንባት ትልቅ ተነሳሽነት በመሆኑ ተሳትፏችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች ገለፁ። በኦሮሚያ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አባላት በሸገር ከተማ መነ አብቹ ክፍለ ከተማ የችግኝ ተከላ መርሃግብር አካሂደዋል። የኦሮሚያ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ዋና ሰብሳቢ ሰለሞን ታፈሰ በዚሁ ወቅት፥ አረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለትውልዱ የተሻለችና ምቹ ሀገርን የመገንባት አጀንዳ በመሆኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራርና አባላትን ጨምሮ ሁሉም ዜጋ በንቃት መሳተፍ እንዳለበት ተናግረዋል። የጋራ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ መሰለፍ ይገባል ያሉት ሰብሳቢው፥ ለአብነትም በልማት፣ በሰላም እና የሀገርን ሁለንተናዊ እድገት ማረጋገጥ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ በጋራ መሰለፍ እንደሚያስፈልግ ነው ያነሱት። መንግስት የተፎካካሪ ፓርቲዎች በዚህ ሂደት እንዲሳተፉ ምቹ ሁኔታን መፍጠሩን ገልጸዋል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ኃላፊ ሞገስ ኢደኤ በበኩላቸው አረንጓዴ አሻራ የፖለቲካ አመለካከት ልዩነት የማይገድበው የጋራ ሀገራዊ አጀንዳ ነው ብለዋል። የፖለቲካ ፓርቲዎች አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ በሀገራዊ ጉዳዮች ተቀራርበው መስራታቸው ለሀገር እድገትና ለዴሞክራሲ ባህል መዳበር አጋዥ መሆኑን ጠቅሰዋል። በኦሮሚያ ክልል የፓለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክርቤት ፀሐፊ ታሪኩ ድንበሩ፥ አረንጓዴ አሻራ ነገን የተሻለ ለማድረግ ትልቅ ተነሳሽነት መሆኑን ገልጸዋል። የገዳ ሥርዓት ለኦሮሞ ነፃነት ፓርቲ ፕሬዝዳንት ሮበሌ ታደሰ፥ አረንጓዴ አሻራ የአንድ ፓርቲ ጉዳይ ሳይሆን የሁሉም ጉዳይ በመሆኑ ተሳትፏችንን አጠናክረን እንቀጥላለን ነው ያሉት። አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የሚያደርጉትን ተሳትፎ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የተናገሩት በኦሮሚያ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሥራ አስፈፃሚ አባል ኤርሚያስ ተገኔ ናቸው።
በአረንጓዴ ዐሻራ የተከልናቸው ችግኞች ለውጤት እንዲበቁ እንንከባከባለን - የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ሰራተኞች
Aug 7, 2025 161
ባህርዳር፤ ነሐሴ 1/2017 (ኢዜአ)፡ -በአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር ላይ በመሳተፍ የተከሏቸው ችግኞች ፀድቀው ለውጤት እንዲበቁ ተከታትለው እንደሚንከባከቡ የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ሰራተኞች ገለጹ። የቢሮውና የተጠሪ ተቋማት አመራሮችና ሰራተኞች በአማራ ህዝብ ዝክረ ታሪክ ማዕከል ቅጥር ግቢ ዛሬ ችግኝ በመትከል አረንጓዴ አሻራቸውን አኑረዋል። በመርሃ ግብሩ ከተሳተፉት መካከል አቶ መልካሙ አዳም በሰጡት አስተያየት፤ በማዕከሉ ግቢ ሀገር በቀል፣ ለምግብነትና ለመድኃኒትነት የሚያገለግሉ ችግኞችን መትከላቸውን ተናግረዋል። የተከሏቸው ችግኞች አካባቢውን ከማስዋብ ባለፈ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቋቋም የሚረዱ፤ ቱሪስቶች የሚያርፉባቸውና ቆይታቸውም ደስተኛ እንዲሆኑ የሚያግዙ መሆናቸውን ገልጸዋል። ችግኞቹ ፀድቀው ለውጤት እንዲበቁም በቀጣይ የአረም፣ ኩትኳቶና ውሃ የማጠጣቱን ተግባር ትኩረት ሰጥተው በማከናወን እንደሚንከባከቡ አስታውቀዋል። ወይዘሮ አስካል አምባቸው በበኩላቸው፤ ዛሬ የተከሏቸውን ችግኞች እንደልጆቻቸው ተንከባክበው ለማሳደግ እንደሚጥሩ ገልጸዋል። ችግኝን ተንከባክቦ ማሳደግ አካባቢን ውብ፣ ሳቢና ማራኪ እንደሚያደርግ ጠቁመው፤ ቀደም ሲል የተከሏቸውን ችግኞችም ተከታትለው በማረምና በመኮትኮት ለውጤት ማብቃታቸውን አውስተዋል። ለምግብነትና ለባህል መድኃኒትነት የሚውሉ ሀገር በቀል ችግኞችን መትከላቸውን የተናገሩት ደግሞ ሌላው የተቋሙ ሰራተኛ አቶ አበበ እምቢያለ ናቸው። የምንተክላቸው ችግኞች የምንተነፍሰው አየር፣ የምንመገበው ምግብና ከህይወታችን ጋር የተቆራኙ በመሆናቸው መትከል ብቻ ሳይሆን ፀድቀው ለውጤት እንዲበቁ እንንከባከባለን ሲሉ ገልጸዋል። የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ መልካሙ ፀጋዬ፤ ዛሬ በአማራ ህዝብ ዝክረ ታሪክ ማዕከል ቅጥር ግቢ የተከሏቸው ችግኞች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው መሆኑን ተናግረዋል። ሀገር የምታንሰራራው፣ በረሃማነትን መከላከል የምንችለው፣ የአፈር መከላትን የምንከላከለውና የምግብ ዋስትናችንን በዘላቂነት ማረጋገጥ የምንችለው ችግኝን በመትከልና ተንከባክበን ስናሳድግ ነው ብለዋል። ዛሬ የተከሏቸው ችግኞች ሀገር በቀልና ለምግብነት፣ ለመድኃኒትነትና ለዕደጥበብ ስራዎች የሚያገለግሉ እንደሆኑ አስረድተዋል፤ ችግኞች የተከሉበት ግቢ አንዱ የቱሪዝም መዳረሻ በመሆኑ ፀድቀው እንዲያድጉ ተንከባክበው የመጠበቁን ስራ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል።