አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
በበልግ ዝናብ ተጠቃሚና ሰብል አብቃይ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚኖረው የዝናብ ሁኔታ ለግብርና ስራ አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል
Mar 12, 2026 76
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 3/2018(ኢዜአ)፦ በቀጣዮቹ አስር ቀናት በበልግ ዝናብ ተጠቃሚና ሰብል አብቃይ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚኖረው የዝናብ ሁኔታ ለግብርና ስራ አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለፀ። ኢንስቲትዩቱ ከመጋቢት 2 እስከ መጋቢት 11 ቀን 2018 ዓ.ም የሚኖረውን የአየር ሁኔታ አዝማሚ አስመልክቶ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፤ በቀጣዮቹ አስር ቀናት ለዝናብ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥሩ የሚቲዎሮሎጂ ገፅታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን የልማት እቅዷ አካል በማድረግ በአካባቢ ጥበቃ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች ትገኛለች በልግ ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት በደቡብ እና በደቡብ ምስራቅ፣ የስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎች፣ የመካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንዲሁም በደቡብ ምዕራብ ላይ የተሻለ ገፅታ እንደሚኖራቸው ይጠበቃል። በዚህም በደቡብ፣ መካከለኛው፣ ምስራቅና እና ሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ይጠበቃል። እነዚህ አካባቢዎች በጥቂት ስፍራዎቻቸው ላይ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ። በዚህም መሰረት ወላይታ፣ ጎፋ፣ ጌዴዮ፣ ጋሞ፣ ባስኬቶ፣ አሪ፣ ኮንሶ፣ ቡርጂ፣ አሌ፣ ጋርዱላ፣ ኮሬ እና ደቡብ ኦሞ ዞኖች እንዲሁም ሁሉም የሲዳማ ክልል ዞኖች ከመካከለኛ እስከ ከባድ የዝናብ መጠን ያገኛሉ ብሏል ኢንስቲትዩቱ። ይህ የዝናብ መጠን በቂ የአፈር እርጥበት እንዲኖር፣ የሰብሎች የውሃ ፍላጎት መሟላት፣ ለቋሚ ተክሎች እድገትና የግጦሽ ሳርና የመጠጥ ውሃ አቅርቦት መሻሻል እንዲኖር በማድረግ ለግብርና ሥራ አዎንታዊ ሚና እንዳለው ጠቅሷል። የአፈር መሸርሸር፣ በሰብል ማሳ ላይ ውሃ መተኛት፣ የሰብል በሽታና ተባይ እንዲሁም የአረም መከሰት ሊያስከትል እንደሚችልም አስጠንቅቋል። ስለሆነም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን መስራት፣ የሰብል በሽታንና አረም እንዳይስፋፋ መከላከል፣ የሰብል ማሳዎችን በቅርበት መከታተልና የአየር ጠባይ ትንበያና ምክረ ሃሳቦችን ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል። በመሆኑም የአየር ሁኔታው አስተዋፅኦ በላቀ ሁኔታ ለመጠቀምና ሊከሰት የሚችለውን አሉታዊ ተጽዕኖ ለመቀነስ የሚቲዎሮሎጂ ምክረ ሀሳቦችን ከወዲሁ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አስረድቷል። በሌላ በኩል በጋምቤላ፣ በአፋር፣ በሶማሌ፣ በቤንሻንጉል-ጉሙዝና በምዕራብ አማራ አካባቢዎች ቀን ላይ ከፍተኛ የሙቀት መጠን እንዲሁም ሌሊት ላይ ወበቅ እንደሚጠበቅ ገልጿል።
በጉጂ ዞን ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን በዘላቂነት ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Mar 11, 2026 76
ነጌሌ ቦረና ፤ መጋቢት 2/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በዘንድሮው ዓመት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን በዘላቂነት ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በኦሮሚያ ክልል የተሻሻሉና የአካባቢን ስነ-ምህዳር ታሳቢ ያደረጉ የቡና ችግኞች ይተከላሉ በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ወንዶ ሸርቦቴ ለኢዜአ እንዳሉት፤በዘንድሮ የክረምት ወቅት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው። የችግኝ ዝግጅቱ በዞኑ ባሉ ከ170 በላይ ችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እየተካሔደ ሲሆን እስካሁን ባለው ሒደት 89 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞችን ለማዘጋጀት መቻሉን አስታውቀዋል። ይህም በየዓመቱ የሚከሰተውን ድርቅና የአካባቢ መራቆት ችግርን በዘላቂነት ለመቋቋም እንደሚያስችል ታምኖበታል ነው ያሉት። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካል የሆነው የችግኝ ዝግጅቱ የጉጂ ዞንን ደጋ፣ ወይና ደጋና ቆላማ የአየር ንብረት ታሳቢ ያደረገ መሆኑን አውስተዋል። ለተከላ ከተዘጋጁት የችግኝ ዝርያዎች ውስጥ ጽድ፣ ግራቪሊያ፣ ወይራ፣ ዋንዛ፣ ዝግባና ሌሎችም እንደሚገኙበት ነው ያመለከቱት። እንዲሁም ለከተማ ውበት፣ ለእንስሳት መኖ፣ ለምግብነት የሚውሉና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው እንደ አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ሙዝና ግሽጣ ያሉ ፍራፍሬዎችን ያካተተ የችግኝ ዝግጅት መደረጉን አስረድተዋል። ችግኞቹን ለማልማትና ለውጤት ለማብቃት ከሰውና ከእንስሳት የተከለለ ከ21 ሺህ 340 ሄክታር በላይ መሬት መዘጋጀቱን አስረድተዋል። በመጪው ክረምት በሚካሄደው የችግኝ ተከላ ስራ ከ205 ሺህ በላይ ህዝብ ለማሳተፍ የቅስቀሳና የግንዛቤ ማሳደግ ስራ እየተካሄደ እንደሚገኝም አመላክተዋል። በዞኑ ባለፈው ዓመት ከተተከሉት ችግኞች በህዝብ እንክብካቤና ጥበቃ 83 በመቶው መጽደቁን በመስክ ምልከታና ክትትል ለማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል።
በክልሉ በበልግ ወቅት እየጣለ ባለው ዝናብ ጎርፍን ጨምሮ የመሬት መንሸራተት አደጋ እያጋጠመ በመሆኑ አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግ ኮሚሽኑ አሳሰበ
Mar 10, 2026 121
አርባምንጭ ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የበልግ ወቅትን ተከትሎ እየጣለ ባለው ዝናብ ጎርፍን ጨምሮ የመሬት መንሸራተት አደጋ እያጋጠመ በመሆኑ ህብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራርና የምግብ ዋስትና ኮሚሽን አሳሰበ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራርና የምግብ ዋስትና ኮሚሽን ኮሚሽነር ወገኔ ብዙነህ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የበልግ ወቅትን ተከትሎ እየጣለ ያለው ዝናብ በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ የጎርፍና የመሬት መንሸራተት አደጋ እያስከተለ ነው። በክልሉ በጋሞ፣ በወላይታ፣ በደቡብ ኦሞ፣ በኮንሶ፣ በጌዲኦ እና በጎፋ ዞኖች በሚገኙ ተራራማ አካባቢዎች ያልተጠበቀ የመሬት መንሸራተት እንዲሁም በአንዳንድ ቆላማ አካባቢዎች ደግሞ የጎርፍ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል አመላክተዋል። ስለሆነም ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ የክልሉ ነዋሪዎች አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባ አሳስበዋል። ህብረተሰቡ በየአካባቢው አጠራጣሪ የሆኑ የመሬት መሰንጠቆች፣ የውሃ ምንጮችና ሌሎች ለውጦች ሲከሰቱ በፍጥነት ለሚመለከተው ክፍል መረጃ በመስጠት ብሎም ስጋት ወደሌለባቸው አካባቢዎች በመሄድ ራሱን ከአደጋው እንዲጠብቅ አስገንዝበዋል። ኮሚሽነር ወገኔ አክለውም በክልሉ የተፈጥሮ አደጋዎችን በዘላቂነት ለመከላከልም በአረንጓዴ አሻራና የተፋሰስ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አስረድተዋል። ከዚህ ቀደም በክልሉ በተለያዩ ዞኖች በተፈጥሮ አደጋ ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን ስጋት ወደሌለባቸው አካባቢዎች በማስፈር መልሶ የማቋቋም ስራ ሲከናወን መቆየቱን አስታውሰዋል። ችግሩን በሳይንሳዊ መንገድ በዘላቂነት ለመከላከል በጥናት ላይ የተመሰረተ ስራ እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል። የጋሞ ዞን አደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መስፍና ማኑቆ በበኩላቸው፤ ትናንት ምሽት በጣለው ከፍተኛ ዝናብ በዞኑ ቦንኬ እና ጋጮ ባባ ወረዳዎች በመሬት መንሸራተት አደጋ የሰው ህይወት ማለፉን ገልጸዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ እና ዙሪያ ወረዳ የኩልፎ እና የሴጎ ወንዞች ሙላት ባስከተሉት የጎርፍ አደጋ በተለያዩ ተቋማትና መሠረተ ልማት ላይ ጉዳት ማድረሱን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የአደጋው መጠን እየተጣራ መሆኑን ጠቁመው ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን መልሶ ለማቋቋም ከነዋሪዎች፣ ከግብረ-ሰናይ ድርጅቶችና ከባለሀብቶች ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን የልማት እቅዷ አካል በማድረግ በአካባቢ ጥበቃ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች ትገኛለች
Mar 10, 2026 116
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን በሀገራዊ የልማት እቅዷ ውስጥ በማካተት በአካባቢ ጥበቃ ረገድ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች መሆኗን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ገለፁ። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ከህንድ የሳይንስና አካባቢ ማዕከል ጋር በመተባበር ያዘጋጁት በሰርኩላር ኢኮኖሚ ላይ የሚያተኩረው 8ኛው የከተሞች ፎረም ከመጋቢት 1 እስከ 3 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) በፎረሙ መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት፣ የሰርኩላር ኢኮኖሚ መርህ የአየር ንብረት የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ እና የ10 ዓመቱ የልማት እቅድ አካል ነው። ስትራቴጂው የኢኮኖሚ እድገትን ከአካባቢ ጥበቃ ጋር ማስተሳሰር፣ ዘላቂ የቆሻሻ አያያዝን እና መልሶ ጥቅም ላይ ማዋልን ማጠናከር እንዲሁም በአረንጓዴ ስራ ፈጠራ በተለይም ወጣቶችንና ሴቶችን ተጠቃሚ ማድረግ ላይ ያለመ ነው ብለዋል። በተጨማሪም በግብርና፣ በምግብ ስርዓት እና በግንባታ ዘርፎች ላይ ያተኮረ ብሄራዊ የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ-ካርታ ወደ ትግበራ መሸጋገሩን ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለምርምር፣ ለቴክኖሎጂ ሽግግር እና ለግል ዘርፉ ተሳትፎ ማዕከል የሚሆን "የሰርኩላር ኢኮኖሚ የልህቀት ማዕከል" በአዲስ አበባ የማቋቋም ሂደት መጀመሯን ገልጸዋል፡፡ ማዕከሉ የሀብት ምርታማነትን በማሳደግ እና በመላው አፍሪካ የአጋርነት ትስስርን በመፍጠር ረገድ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረውም ጠቅሰዋል፡፡ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፋንታ ደጀን በበኩላቸው በኢትዮጵያ የከተማ ልማት ስራዎች ከአካባቢ ጥበቃ ጋር ተሰናስለው እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። የሰርኩላር ኢኮኖሚ ከተሞች ሀብትን በብክነት ፈንታ ወደ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እንዲቀይሩ የሚያስችል ማዕቀፍ መሆኑን አስገንዝበዋል። በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩመር ራይ በአፍሪካ እየታየ ላለው ፈጣን የከተሞች መስፋፋት ተስማሚ የአካባቢ ጥበቃ መፍትሄዎች እንደሚያስፈልጉ ገልጸዋል። በዚህም ኢትዮጵያ በኮሪደር ልማት እያከናወነች ያለው ተግባር ለሌሎች ሀገራት ትልቅ ትምህርት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መሪነት የተከናወኑ የልማት ስራዎች ከተማን እንዴት መለወጥ እንደሚቻል በተግባር ማሳየት መቻሉን ጠቅሰው አዲስ አበባ አሁን ላይ ሰፋፊ መንገዶች፣ የብስክሌት መጓዣያዎች እና አረንጓዴ ስፍራዎች ያሏት ዘመናዊ ከተማ መሆኗን ጠቁመዋል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል
Mar 9, 2026 152
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30 /2018(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር ማስቻላቸውን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ። የኢትዮጵያ የአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ተምሳሌታዊ ተግባር ነው የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ ፈጠራና የሕግ ተከባሪነት ስኬታማ ስራ ተሰርቷል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶችም የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ለፅዱ ኢትዮጵያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ገልጸዋል። የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የፕላስቲክ፣ የአፈር፣ የውሃ፣ የአየርና የድምፅ ብክለትን በመከላከል የአካባቢና ማህበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ ላይ ትኩረት ማድረጉን ተናግረዋል። በንቅናቄው መሠረት በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ15 ሚሊየን በላይ ከሚሆን ህዝብ ጋር የገፅ ለገፅ መድረክ በመፍጠር የአካባቢ ጥበቃና ፅዱ አካባቢ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት መሰጠቱን አንስተዋል። በመገናኛ ብዙሃንም ከ50 ሚሊየን በላይ ህዝብ ተደራሽ በማድረግ ህብረተሰቡ በአካባቢ ላይ የሚደርስ ብክለትን መቀነስ የሚያስችል የዕውቀት፤ የግንዛቤና የሕግ ማስከበር ሥራ መሰራቱን አስረድተዋል። በዚህም በሁለት ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የዜጎችን የአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ በማሳደግ ፅዱና የበለፀገች ኢትዮጵያን ለትውልድ ማስተላለፍ የሚያስችል መሰረት መጣሉን ጠቅሰዋል። በቀጣይም 3ኛ ዙር የፅዱ ኢትዮጵያን ባህል እናድርግ ሀገር አቀፍ ንቅናቄ ለማስጀመር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። በ3ኛው ዙር ሀገር አቀፍ ንቅናቄም የለውጡን ዓመታትን የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች በማጽናት ባህል ይሰራል ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተተገበሩ የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የገጠርና ከተማ ኮሪደር ልማት ስኬቶች የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ለፅዱ ኢትዮጵያ ግንባታ ወሳኝ ሚና እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል። የኮሪደር ልማት ስራ የፍሳሽ አወጋገድና የቆሻሻ አያያዝን በማዘመን ዜጎችን ፅዱ የመኖሪያ ምኅዳር በማጎናጸፍ የወንዞችን ጤናማነት የሚያስጠብቅ ተምሳሌታዊ የልማት ስኬት መሆኑንም ተናግረዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃና የእርከን ሥራ የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በማስጠበቅ ገንቢ ሚና እየተወጣ እንደሚገኝ አንስተዋል። በሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታም ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚሰሩ የግሉን ዘርፍ ማበረታታት የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑንም አመላክተዋል።
በጋምቤላ ክልል የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Mar 9, 2026 176
ጋምቤላ ፤ የካቲት 30 /2018(ኢዜአ)፦በጋምቤላ ክልል የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ አለሚቱ ኡሞድ ገለፁ። በክልሉ ኮንትሮባንድ እና ህገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን በመከላከል ጤናማ የገበያ ሥርአት ለመፍጠር ትኩረት ተሰጥቷል በክልሉ በዘንድሮው ዓመት እየተካሄደ ባለው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማትና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች የማጠናከሪያ መርሃ ግብር በጎግ ወረዳ እየተካሔደ ነው። ርዕሰ መስተዳደሯ አለሚቱ ኡሞድ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ፤የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የጎላ ድርሻ አላቸው። ይህን ታሳቢ በማድረግ በተራቆቱ አካባቢዎች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በማጠናከር በክልሉ የተጀመረውን የግብርና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ስኬታማ ለማድረግ በትኩረት መስራቱ ይቀጥላል ብለዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተፋሰስ ልማትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የአካባቢ መራቆትንና የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል በኩል እመርታዊ ለውጥ እንዲመጣ እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም የተጀመረው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ በሁሉም አካባቢዎች ተጠናክሮ እንዲቀጥል አመራሩ በቁርጠኝነት መስራት ይገባዋል ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤልያስ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመላቀቅ ለተቀመጠው ግብ መሳካት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች የላቀ አበርክቶ አላቸው። ባለፉት አመታት ለተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች በተሰጠው ትኩረት የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙና የግብርና ምርታማነት እንዲጨምር ማስቻሉን ተናግረዋል። በመሆኑም የተፈጥሮ ሃብትን መሠረት ያደረገ የግብርና ልማትን ለማስፋት የተጀመረው ጥረት በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የጋምቤላ ክልልም ለግብርና ልማት የተመቸ ስነ ምህዳር ያለው አካባቢ መሆኑን ጠቅሰው ይህንን ሃብት በአግባቡ አልምቶ ከመጠቀም አንፃር የቅንጅት ስራዎች እንደሚጠናከሩ ገልፀዋል። በክልሉ ሲከናወን በቆየው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር እርጥበታማነትንና ለምነትን በማሻሻል የሰብል ምርታማነትን እያሳደገ ይገኛል ያሉት ደግሞ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንድሮው ቱት ናቸው። በክልሉ የተፋሰስ ልማትን በማጠናከር የከርሰ ምድርና የገፀ ምድርን የውሃ ሀብት በማሻሻል የግብርና ልማቱን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ነው የተናገሩት። በክልሉ በዘንድሮዉ የተፋሰስ ልማት ስራ በሁሉም ወረዳዎች በ101 ተፋሰሶች፤ 64 ሺህ ሄክታር የተራቆተ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ከቢሮው የተገኘ መረጃ ያመለክታል ።
የአባያና ጫሞ ሀይቆችን ከስጋት መታደግ የሚያስችል የተቀናጀና በጥናት የተደገፈ ስራ ይሰራል
Mar 7, 2026 170
አርባ ምንጭ፤ የካቲት 28/2018 (ኢዜአ)፦ የስምጥ ሸለቆ ተፋሰስ የሆኑ የአባያና ጫሞ ሀይቆችን ከስጋት ለመታደግ የተቀናጀና በጥናት የተደገፈ ስራ እንደሚሰራ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ አስተባባሪነት የአባያና ጫሞ ሀይቆች የሚያስከትሉትን ተጽእኖ መቀነስ የሚያስችል የባለድርሻ አካላት ውይይት በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ነው። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በዚህ ጊዜ እንደገለጹት የአባያና ጫሞ ሀይቆችን በአግባቡ መጠቀም ባለመቻሉ ከፀጋነት ወደ ስጋትነት እየተቀየሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በተለይ በጋሞ፣ በጋርዱላ፣ በኮንሶና በቡርጂ ዞኖች የሚገኙ አርሶ አደሮችን ማሳ እንዲሁም በተለያዩ መሠረተ ልማቶች ላይ አደጋ እያስከተሉ ይገኛሉ ብለዋል። በመሆኑም ሐይቆቹን ከስጋት ለመታደግ የተቀናጀና በጥናት የተደገፈ ስራ እንደሚጠናከር ገልጸዋል፡፡ ተፋሰሶቹ የተፈጥሮ ስነ-ምህዳር፣ የፍራፍሬ፣ የብዝሃ ህይወት የቱሪዝምና የቀጣናዊ ልማት ማሳለጫዎች መሆናቸውን ጠቅሰው ከስጋት ወደ ሀብት ምንጭነት ለመቀየር የባለድርሻ አካላት ሚና ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። በውሃው ዘርፍ የረጅም ጊዜ ልምድ ያለው አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉን ችግሮች ለመቅረፍ እያደረገ ያለውን ጥረት አድንቀው የክልሉ መንግስት የበኩሉን እንደሚወጣም አረጋግጠዋል። የማዕድን ሚኒስትርና የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሰብሳቢ ኢንጂነር ሀብታሙ ተገኝ በበኩላቸው የአባያና ጫሞ ሃይቆችን በዘላቂነት መጠቀም ለሃገር ሁለንተናዊ ብልጽግና ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ በአርባ ምንጭና አካባቢው መልከ ብዙ ፀጋዎች መኖራቸውን ጠቅሰው የሀይቆቹን ትሩፋት ለማጉላት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ በአግባቡ ሊከናወን እንደሚገባ ጠቁመዋል። በተገኙ ጥናቶች መሠረት የተፋሰሶቹን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት የተለያዩ ፕሮግራሞች፣ ስትራቴጂዎችና ፕሮጀክቶች ተቀርጸው መተግበር እንዳለባቸውም አመልክተዋል። የአባያና ጫሞ ሀይቆች የውሃ መጠን መጨመር፣ የተፋሰሱ ወንዞች ሙላትና ደለል ከፍተኛ አካባቢያዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖዎችን እያስከተሉ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት አብደላ ከማል(ዶ/ር) ናቸው። የአባያና ጫሞ እንዲሁም ሌሎች ተፋሰሶች በተቀናጀ ሁኔታ ካልተመሩ ተጽዕኖው ከሀይቆቹ ዳርቻ አልፎ ሰፊ ቦታዎችን ሊያዳርስ እንደሚችል በጥናት መረጋገጡንም ጠቅሰዋል። ዩኒቨርሲቲው በተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ምክንያቶች የሚከሰቱ ተግዳሮቶችን በሳይንሳዊ መንገድ ለመከላከል የጀመረውን ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል። በመድረኩ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የስራ ኃላፊዎችና ተመራማሪዎች፣ ባለሀብቶች፣ የጋሞ ሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶችና ሌሎችም እየተሳተፉ ነው።
የኢትዮጵያ የአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ተምሳሌታዊ ተግባር ነው
Mar 7, 2026 140
አዲስ አበባ፤ የካቲት 28/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራን ጨምሮ በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና (Climate-smart agriculture) አርአያ የሚሆን ስራ እያከናወነች እንደምትገኝ የዓለም ባንክ ከፍተኛ የግብርና ባለሙያ ቲም ሮበርትሰን ገለጹ። ለአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና (Climate-smart agriculture) ሁሉን አቀፍ እይታ ያለው የግብርና ምርታማነት አማራጭ መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ይገልጻሉ። የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት ይጠበቅባቸዋል ይህ የአሰራር ዘዴ የግብርና ምርታማነት ብቻ ሳይሆን ለአደጋዎች የማይበገር አቅም መገንባትና ለአየር ንብረት ተስማሚ መሆን እንዳለበት ያስቀምጣል። ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነች ትገኛለች። ድርቅን የሚቋቋሙ ሰብሎችን ማምረት፣ አረንጓዴ አሻራ፣ የስንዴ ምርታማነት፣ የኢትዮጵያ የማዳበሪያ እና የጤናማ አፈር ፍኖተ ካርታ፣ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን የመስኖ ስራዎች ማስፋትና የተራቆቱ መሬቶችን በአካባቢ ጥበቃ ስራ ወደ ነባር ይዞታቸው መመለስ ከተከናወኑ ተግባር መካከል ይጠቀሳሉ። የዓለም ባንክ ከፍተኛ የግብርና ባለሙያ ቲም ሮበርትሰን ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና እየገነባች ያለችው አቅም የሚደነቅ መሆኑን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ስኬታማ ስራዎችን እያከናወነች እንደሚገኝ ጠቅሰው እንደ አረንጓዴ አሻራ ባሉ ኢኒሼቲቮች የቀጣናው ሀገራት ተጠቃሚ ሊሆኑ እንደሚገባ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የዘርፉ ስኬቶች ለማስፋት መንግስት፣ ቀጣናዊ ተቋማት እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ይበልጥ ተቀራርበው መስራት እንዳለባቸውም አመልክተዋል። ኢትዮጵያን ጨምሮ በቀጣናው የሚገኙ ሀገራት በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ያላቸውን አቅም የበለጠ ማጠናከር እንደሚኖርባቸውም ነው ባለሙያው የገለጹት። በዚህ ረገድ የዓለም ባንክ ከመንግስታት ጋር የግሉ ዘርፍ በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ያለውን የኢንቨስትመንት ተሳትፎ ለማሳደግና በተለይም ለወጣቶች የስራ ዕድል ለመፍጠር እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ኢኖቬሽን፣ ዲጂታል መፍትሄዎች፣ ዘላቂ የኢነርጂ አጠቃቀም እና ለአየር ንብረት ተስማሚ ግብርናን ማሳደግ ወሳኝ መሆኑንም ነው ያነሱት። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የዓለም የግብርና ፋይናንስ ከፍተኛ ለውጥ ማሳየቱን ገልጸው ሀገራት ፋይናንስ በዘላቂነት የሚያመጡ አጋርነቶችን መፍጠር እንዳለባቸው መክረዋል። ለዚህ ተቋማት ትስስራቸውን ማጠናከር፣ አማራጭ ፋይናንስ መፈለግ፣ እሴት መጨመር ትኩረት መስጠት እና ለጋራ ግብ በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል።
በጋምቤላ ክልል ወይና ደጋማ አካባቢዎች የሚኖረው የዝናብ ስርጭት ለበልግ እርሻ አመቺ ነው
Mar 6, 2026 265
ጋምቤላ ፤ የካቲት 27/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል ወይና ደጋማ አካባቢዎች በቀጣዮቹ ሶስት ወራት የሚኖረው የዝናብ ስርጭት ለበልግ እርሻ አመቺ መሆኑን በኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የጋምቤላ ክልል ሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል አስታወቀ። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ሀገራት ለዓለም አቀፍ ቃል ኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል በኢንስቲትዩቱ የጋምቤላ ክልል የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ ተስፋሁን ዓለሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ወይና ደጋማ አካባቢ በቀጣይ ወራት የሚኖረው የበልግ ዝናብ ለእርሻ ስራ ተስማሚ ነው። በክልሉ ወይና ደጋማ የአየር ፀባይ ያለው የማጃንግ ዞን በቀጣዩቹ ሶስት ወራት የሚኖረው የዝናብ ስርጭት ለእርሻ ስራና ለእንስሳት ግጦሽ አመቺ ሁኔታን እንደሚፈጥር የአየር ትንበያ መረጃ ያመለክታል ብለዋል። በተለይም በዞኑ ቀድመው ለሚዘሩ የሰብል ዓይነቶችና ለመኸር እርሻ ስራ ዝግጅት በቂ የዝናብ ስርጭት እንደሚኖር መተንበዩን አመላክተዋል ። በሌላ በኩል ደግሞ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት በክልሉ ቆላማ አካባቢዎች ጠንከር ያለ የሙቀት መጠን እንደሚኖር የትንበያ መረጃዎች እንደሚያሳዩ ገልጸዋል። በመሆኑም የከርሰ ምድርና የገጸ ምድር የውሃ መጠን መቀነስ ሊኖር ስለሚችል ህብረተሰቡ ውሃን በአግባቡ መጠቀም እንዳለበት ምክር ሃሳብ ሰጥተዋል። እንዲሁም ከሙቀቱ መጨመር ጋር ተያይዞ በሰዎች ላይ የቆዳ ሽፍታ ሊከሰት ስለሚችል ማህበረሰቡ ጥንቃቄ ሊያደርግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ሀገራት ለዓለም አቀፍ ቃል ኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል
Mar 5, 2026 181
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018 (ኢዜአ)፡-የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አስከፊ ተፅዕኖ ለመቀነስ ሀገራት ለዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃል ኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ገለጸ። የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት ይጠበቅባቸዋል ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ተፈፃሚነት ያላት ቁርጠኝነት ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ እንዳስቻላት በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአየር ንብረት ተቋማዊ ልማት አማካሪ መንሱር ደሴ ገልጸዋል። ከየካቲት 23/2018 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ አራት ቀናት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና የአውደ ጥናት የምክክር መድረክ ተጠናቋል። በአውደ ጥናቱ ማጠናቀቂያ ላይ የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ፤ የአካባቢና የሥነ-ምኅዳር ደኅነንት ለማስጠበቅ ትብብርን ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል። አውደ ጥናቱም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ተግባራዊ የተደረጉ መርሃ ግብሮችና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ስኬታማ የልምድ ልውውጥና ግብዓት እንደተገኘበት ገልጸዋል። በፖሊሲዎችና የትኩረት መስኮች የተደረገው ውይይትም የዕውቀት ሽግግር የተደረገበት መሆኑን ተናግረዋል። ዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የመንግሥታቱን ድርጅት የአየር ንብረት ስምምነት መነሻ በማድረግ ለተለያዩ ሀገራት የገንዘብ ድጋፍ እያቀረበ እንደሚገኝ አንስተዋል። ሀገራትም የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አስከፊ ተፅዕኖ ለመቀነስ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚያደርጉትን ጥረት እንደሚያግዝ አረጋግጠዋል። በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአየር ንብረት ተቋማዊ ልማት አማካሪ መንሱር ደሴ በበኩላቸው፤ በአውደ ጥናቱ ከ14 የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ 150 ሙያተኞች መሳተፋቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ትግበራ ያላት ቁርጠኝነት በልማት አቅጣጫዎቿ ላይ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን አስረድተዋል። በአውደ ጥናቱም ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በተደረገ ድጋፍ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች በተሞክሮነት መቅረባቸውን ተናግረዋል። ከሀምሌ ወር ጀምሮ ለአራት ዓመታት የሚተገበረው የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም መርሃ ግብርም ከኢትዮጵያ የልማት አቅጣጫዎች ጋር ተጣጥመው እንደሚተገበሩ አንስተዋል።
በምስራቅ ሸዋ ዞን የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት ያደረጉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Mar 4, 2026 252
አዳማ ፤ የካቲት 25/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት ያደረጉና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማፍላት ስራ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ ነው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ሃገራዊ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ሐምሌ 2011 ዓ.ም መጀመሩ ይታወቃል። በምስራቅ ሸዋ ዞን ግብርና የጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በዞኑ 11 ወረዳዎች ባሉ የችግኝ ማፊያ ጣቢያዎች ለመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ ተጀምሯል። ችግኝ ጣቢያዎቹ ለአረንጓዴ አሻራ ዘመቻው የተለያየ ዝርያ ያላቸው ችግኞችን አፍልቶ በማቅረብ ረገድ እያበረከቱ ያለው አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን አስታውሰዋል። ዘንድሮም ለማዘጋጀት ከታቀደው ከ284 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ውስጥም 241 ነጥብ 4 ሚሊዮን ችግኞችን የማፍላት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። ቀሪ ችግኞችን የማፍላት ሥራም እስከ መጪው ግንቦት ወር ድረስ ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በችግኝ ዝግጅቱም በአብዛኛው የአየር ንብረት መዛባትን ለመከላከል ለሚያገለግሉ የደን እና ጥምር ደን ዝርያዎች ትኩረት የተሰጠ መሆኑን አስረድተዋል። በተጨማሪም ለአርሶ አደሩ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን የሚያስገኙና እና ለምግብነት የሚውሉ 26 ነጥብ 7 ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኞችን ያካተተ የዘር ዝግጅት መደረጉንም ተናግረዋል። የዘንድሮ ዓመት የችግኝ ተከላ የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት በማድረግ የሚከናወን መሆኑን ጠቁመው በዞኑ ባለፉት ዓመታት ከተተከሉ ችግኞች ከ85 በመቶ በላይ መጽደቃቸውን አስታውቀዋል። በአሁኑ ወቅትም የተተከሉ ችግኞችን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ የመጠበቅና የመንከባከብ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ነው ያረጋገጡት። በዘንድሮው ዓመት በዘርፉ የተቀመጠውን እቅድ ለማሳካትም የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ተቆፍረው መዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል።
የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት ይጠበቅባቸዋል
Mar 3, 2026 229
አዲስ አበባ፤ የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፦የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት እንደሚጠበቅባቸው የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) ገለጸ። "በምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ የሚቋቋም ግብርናን ማስፋፋት" በሚል መሪ ሃሳብ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ቀጣናዊ የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። በኢጋድ፣ የዓለም ባንክ የአፍሪካ ቢሮ፣ የሥርዓተ ምግብ ፕሮግራም ለምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ፣ የደቡባዊ አፍሪካ የግብርና ምርምርና ልማት ማስተባበሪያ ትብብር በተዘጋጀው መድረክም የግብርና ማሻሻያ ምክረ ሀሳቦችን እንደሚያፈልቅ ይጠበቃል። የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) ተወካይ ዳህር ኤልሚ፤ በአየር ንብረትና በሥነ-ምኅዳር ደኅንነት የሚከሰት ለውጥ የግብርና ምርታማነት ላይ ጫና እያሳደረ ነው ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለው የአፈር መራቆት፣ ድርቅ፣ ጎርፍ፣ ዝናብ እጥረትና በርሃማነት የምስራቅ አፍሪካ የግብርና ምርታማነትና የምግብ ፍጆታ ላይ አሉታዊ ጫና እንደሚያሳድሩ ገልጸዋል። በዚህም የቀጣናው ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት ለመገንባት የቴክኖሎጂ፣ የግብዓትና የመረጃ ትንተና አቅም መገንባት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣንም የቀጣናውን ሀገራት የግብርና ምርታማነት የሚያሻሽል የአየር ሁኔታ የመረጃ ትንተና ተደራሽ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት የተፈጥሮ ሃብትና የአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ፕሮግራም ዳይሬክተር አወቀ ሙሉዓለም በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ሥርዓት ውጤት እያስመዘገበ ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችም የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ በማድረግ የአርሶና አርብቶ አደሩን የግብርና ምርታማነት እያሳደገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዓለም ባንክ ከፍተኛ የግብርና ባለሙያ ቲም ሮበርትሰን፤ የግብርና ምርታማነት የሚያዘምኑ የፋይናንስና የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በማስፋት የቀጣናው ሀገራት አርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል። በኢትዮጵያ የኒውዝላንድ አምባሳደር የኢጋድና የአፍሪካ ሕብረት ቋሚ ተወካይ አምባሳደር ኦሊቪያ ኦዌን በበኩላቸው፤ የግብርና ምርታማነትን ማረጋገጥ ለአፍሪካ ዕድገትና ብልጽግና ወሳኝ ነው ብለዋል። የቀጣናውንና አፍሪካን የግብርና ሥርዓት ለማዘመን በሚደረገው ጥረትም የኒውዝላንድ መንግስትና የልማት አጋሮች የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በፎረሙ ላይ የኢጋድ አባል ሀገራት ተወካዮች፣ ፖለሲ አውጪዎች፣ የልማት አጋሮች፣ የግሉ ዘርፍ ተወካዮችና ተመራማሪዎች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ስርጭትና መጠን ይጠናከራል
Mar 3, 2026 168
አዲስ አበባ፤ የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፦በቀጣዮቹ አስር ቀናት በሀገሪቱ የበልግ ሰብል አብቃይ አካባቢዎች የዝናብ መጠንና ስርጭት በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋና እየተጠናከረ እንደሚሄድ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ አራተኛውን የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስራ ሊያስጀምር ነው በኢንስቲትዩቱ የሚቲዎሮሎጂ ትንበያ፣ምክር አገልግሎት እና ምርምር ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አሳምነው ተሾመ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለዝናብ መፈጠር ምቹ የሆኑ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች ይበልጥ እየተጠናከሩ መሆናቸውን የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ። የዝናብ ስርጭቱ የሚሸፍናቸው ደቡብና ደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያ (ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው የሆኑ አካባቢዎች)፣ የስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎች፣ የመካከለኛውና የደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች ምስራቅና ሰሜን ምስራቅ አካባቢዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። በእነዚህ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ የሚጠበቅ ሲሆን፣ በአብዛኛው ስፍራዎች የዝናብ መጠኑ መደበኛና ከመደበኛ በላይ እንደሚሆን ገልጸው፤አልፎ አልፎም ከባድ ዝናብ ሊኖር እንደሚችል ተናግረዋል። የዝናቡ መሻሻል በተለይም ለበልግ አብቃይ አርሶ አደሮች ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል። በበልግ እየጣለ ያለው ዝናብ የማሳ ዝግጅትና ዘር፡ የአፈር እርጥበትን በማሻሻል አርሶ አደሩ የተለያዩ ሰብሎችን መዝራት እንዲችል ምቹ ሁኔታን በመፍጠር አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። ለቋሚ ተክሎች፡ ቀደም ብለው ለተዘሩ የበልግ ሰብሎችና በአካባቢው ለሚገኙ ቋሚ ተክሎች ዕድገት ያለውን አስተዋጽኦም ገልጸዋል። ለውሃ አጠር አካባቢዎችም አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ የሚጥለውን የዝናብ ውሃ በማሰባሰብና በማከማቸት ለቀጣይ እንዲጠቀም ምክረ ሀሳብ አቅርበዋል። በበልግ የሚጥለው ዝናብ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የገጸ ምድር ውሃ መጠን በተለያዩ ተፋሰሶች ላይ እንደሚጨምርም ገልጸዋል። በዚህም ኦሞ ጊቤ፣ ስምጥ ሸለቆ፣ የላይኛውና መካከለኛው አዋሽ፣መካከለኛና ታችኛው አባይ፣ ገናሌ ዳዋ እና ዋቤ ሸበሌ ተፋሰሶች የተሻለ እርጥበት እንደሚያገኙ ይጠበቃል ብለዋል። በዚህም የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የውሃ ማጠራቀሚያዎችን በመጠቀም የውሃ መጠናቸው ከፍ እንዲል ያደርጋል ብለዋል። ከዚሁ ጋር በተያያዘ በአንዳንድ የአገሪቱ ክፍሎች አሁንም ከፍተኛ የቀን ሙቀት እንደሚቀጥል ገልጸዋል። በዚህም በጋምቤላ፣ አፋር፣ ሶማሌ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝና ምዕራብ አማራ አካባቢዎች የቀኑ ከፍተኛ ሙቀት ከ33 እስከ 37 ነጥብ 2 ዲግሪ ሴልሺየስ ሊደርስ እንደሚችል የትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ ተብሏል።
ኢንስቲትዩቱ አራተኛውን የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስራ ሊያስጀምር ነው
Mar 3, 2026 145
ዳንቦያ፤ የካቲት 24/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣ ከንባታ ዞን አራተኛውን ዘመናዊ የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር የመትከል ተግባርን በማጠናቀቅ ስራ ለማስጀመር የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ እንደሚገኝ አስታወቀ። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ እንደገለጹት፤ ኢንስቲትዩቱ በክልሉ ከንባታ ዞን ዳንቦያ ወረዳ ዳቶ ዳርሀቦራ ተራራ ላይ ነው ዘመናዊ የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳሩን የተከለው። ራዳሩ በ250 ኪሎ ሜትር ራዲየስ ውስጥ ያለን የአየር ሁኔታ መረጃ የመሰብሰብ አቅም ያለው ሲሆን፣ የትንተናና የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራዎችን በተሻለ ጥራት ለመከወን ያስችላል ብለዋል። በ14 ሜትር ከፍታ ላይ የተተከለው ይህ ራዳር የዝናብ መጠንን፣ የንፋስ ፍጥነትን፣ የዳመና እንቅስቃሴንና ዝናብ ያዘለ አውሎ ነፋስን የመሳሰሉ መረጃዎችን ከርቀት በመቃኘት ለዋናው የዳታ ማዕከል መረጃ ያስተላልፋል ብለዋል። ይህ የራዳር ጣቢያ በኢትዮጵያና በፊንላንድ መንግሥታት ድጋፍ 13 ሚሊዮን ዩሮ በሚጠጋ በጀት ወደ ሥራ ከሚገቡ ፕሮጀክቶች አንዱ መሆኑን የገለፁት ዳይሬክተሩ፤ አገልግሎቱን በቴክኖሎጂ ለማዘመንና የተሳለጠ መረጃ ለማቅረብ ትልቅ ፋይዳ እንዳለውም አብራርተዋል። በፕሮጀክቱ የተጠቀሰውን ጨምሮ አራት የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳሮች፣ 10 የአየር ብክለት መከታተያ ጣቢያዎች፣ 10 የመብረቅ መከታተያና ሌሎች የተቀናጁ የሚቲዎሮሎጂ መሠረተ ልማትን የመገንባት ሥራን ያካተተ ነው ብለዋል። ኢንስቲትዩቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ በ12 ስልታዊ ቦታዎች ላይ የራዳር ጣቢያዎችን ለመትከል እቅድ መያዙን ጠቁመው፤ አራተኛውን ጣቢያ በማጠናቀቅ የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎቱን የማሳደግ አቅሙን አንደሚያጠናከር አስረድተዋል። ራዳሩ በተተከለበት አካባቢ የኃይል መቆራረጥም ሆነ የመረጃ ልውውጥ እንዳይቋረጥ የፀሐይ ብርሃን ኃይል (ሶላር ኢነርጂ) እየተገጠመ ይገኛል ብለዋል። የፕሮጀክቱን የመጨረሻ ምዕራፍ ለመጎብኘት በስፍራው የተገኙት በፊንላንድ ኤምባሲ የትብብር ዘርፍ ኃላፊ ቶሚ ሳርኪኦጃ መንግሥታቸው የኢትዮጵያን ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በመደገፉ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል።
በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ ነው
Mar 3, 2026 121
ነጌሌቦረና፤የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ ኩልሌ ሸና እንደገለጹት፤ ዞኑ ቆላማና ዝናብ አጠር በመሆኑ በየጊዜው የሚያጋጥመውን የእንስሳት መኖ እጥረት በዘላቂነት ለመቋቋም ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። ለዚህም በዘንድሮው የበጋ ወቅት ሕብረተሰቡን በማሳተፍ 105 ተፋሰሶችን መሠረት ያደረገ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል። በዞኑ በሁሉም ወረዳዎች በሚገኙ ተፋሰሶች ላይ የሚካሄደው የተቀናጀ የልማት ሥራ ከ52 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት የሚያካልል መሆኑን አቶ ኩልሌ ጠቁመዋል። ከዚህ ውስጥ በሰው ሰራሽ ጫና እና ከልክ ያለፈ ግጦሽ የተራቆተ ከ38 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ተከልሎ መልሶ እንዲያገግም እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በተከናወነው እንቅስቃሴ 24 ሺህ 430 ሄክታር የግጦሽ መሬት ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተከልሎ እንዲያገግም የተደረገ ሲሆን፣ ይህም መኖን በዘላቂነት ለማግኘት የሚደረገውን ጥረት ያግዛል። ከተፈጥሮ ግጦሽ በተጨማሪም በክረምትና በበጋ መስኖ የታገዘ የመኖ ልማት ለማስፋፋት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ምክትል ኃላፊው አስታውቀዋል። በዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ከተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት መካከል የአፈርና የድንጋይ እርከን እንዲሁም የጎርፍ መፋሰሻ ቦይ ግንባታ እየተከናወነ ሲሆን የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ዝግጅትንም ጠቅሰዋል። በነዚህ የልማት ሥራዎች ላይ አርሶና አርብቶ አደሮች፣ የወጣቶችና የሴቶች አደረጃጀቶች በንቃት ተሳትፈዋል። ከዚህም ባለፈ በበልግና በክረምት የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማዘጋጀት ሥራ እየተከናወነ መሆኑ ተገልጿል። የሊበን ወረዳ የጎቢቻ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ወርቁ አለባቸው በሰጡት አስተያየት፤ አካባቢያቸው ዝናብ አጠር በመሆኑ በተደጋጋሚ ለሚከሰተው የእንስሳት መኖ እጥረት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት ከደረሰባቸው ጉዳት በመማር አሁን ላይ በአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ላይ በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛው የቀበሌው ነዋሪ አቶ አልዬ ኢብራሂም በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ አሻራ እና የእንስሳት መኖ ልማት ለአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ የህልውና ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰው፤ ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም በአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ላይ ቅድሚያ በመስጠት እንደሚሳተፉ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ ናቸው
Mar 2, 2026 147
አዲስ አበባ፤ የካቲት 23/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና አውደ ጥናት በአዲስ አበባ ተካሂዷል። የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት እንዳሉት የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በዓለም ደረጃ የአካባቢ መራቆትን፣ የብዝሃ ህይወት መመናመንን እንዲሁም በትልልቅ የውሀ አካላት ላይ እየደረሱ ያሉ ጉዳቶችን ለመከላከል ድጋፍ የሚያደርግ ዓለም አቀፍ ተቋም ነው። ተቋሙ ለሚቀጥሉት አራት ዓመታት የሚሆን ፕሮግራም ተግባራዊ እንደሚያደርግ ገልጸው የአውደ ጥናቱ ዓላማ ከዚህ ቀደም የተተገበሩ ፕሮግራሞችን ለመገምገም መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ እና የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ረገድ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ተግባራዊ መደረጋቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በእነዚህ ስራዎች አማካይነት እውቅና እያገኘችበት እንደምትገኝም ገልጸዋል። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ በበኩላቸው የምስራቅ አፍሪካ ሰፊ የተፈጥሮ ሀብት እና እምቅ አቅም እንዳለው ጠቅሰው፥ ይሁን እንጂ እንደ ብዝሃ-ህይወት መጥፋት፣ የመሬት መራቆት እና ብክለት ያሉ ፈተናዎች የተደቀኑበት ቀጣና ነው ብለዋል። በመሆኑም ቀጣናዊና፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት በአየር ንብረት ለውጥ የሚደርሱ ጫናዎችን ለመቋቋም በትብብር መሥራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በተለያዩ መንገዶች የገንዘብ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ከዘላቂ ልማትና ከአረንጓዴ የኢኮኖሚ እድገት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ እርምጃዎችን እየወሰደች ነው
Mar 2, 2026 169
አዲስ አበባ፤ የካቲት 23/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ከዘላቂ ልማትና ከአረንጓዴ ኢኮኖሚ እድገት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ እርምጃዎችን እየወሰደች መሆኑን የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና አውደ ጥናት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማትና በታዳሽ ኃይል ለዓለም የስኬት አርዓያ ሆናለች -የሮማኒያ አምባሳደር የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት፥ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የሥነ-ሕይወት መጥፋት እና ብክለት በምድራችን የአካባቢ ደህንነት፣ የምግብ ዋስትና እና የልማት ጉዞ ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይ በምስራቅ አፍሪካ የሚከሰቱ ድርቅና የአካባቢ መራቆት በማህበረሰቡና በስርዓተ ምህዳሩ ላይ አስከፊ ጉዳት እያስከተሉ እንደሚገኙ ገልጸዋል። አካባቢን መጠበቅና የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የህልውና ጉዳይና የብልጽግና መሰረት መሆኑን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመከላከል ለአፍሪካና ለዓለም ምሳሌ የሚሆን አኩሪ የአረንጓዴ ልማት ተግባራትን እያከናወነች እንደምትገኝ ተናግረዋል። ከዘላቂ ልማትና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ከመገንባት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎቿ ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑንም ጠቅሰዋል። በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በሰባት ዓመታት ውስጥ ብቻ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ታላቅ የደን ልማት ለዓለም ማሳየቷንም አንስተዋል። እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ያሉ የታዳሽ ሃይል ልማት ፕሮጀክቶች፣ የከተሞች የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ ልማት፣ የሌማት ትሩፋት፣ የበጋ መስኖ ስንዴ እና ሌሎችም የልማት ኢኒሼቲቮች ከራሷ አልፎ ለቀጣናው ዘላቂ ዕድገት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል። የአውደ ጥናት የምክክር መድረኩ በአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ዙሪያ የትብብር ሥራዎችን በማስፋት የጋራ ዕድገትን ለማረጋገጥ የሚበጁ ምክር ሀሳቦችን ለማመንጨት እንደሚረዳ አንስተዋል። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ በበኩላቸው፤ ምስራቅ አፍሪካ ሰፊ የተፈጥሮ ሀብት እና እምቅ አቅም እንዳለው ጠቅሰው፥ ይሁን እንጂ እንደ ብዝሃ-ህይወት መጥፋት፣ የመሬት መራቆት እና ብክለት ያሉ ፈተናዎች የተደቀኑበት ቀጣና ነው ብለዋል። በመሆኑም ቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት በአየር ንብረት ለውጥ የሚደርሱ ጫናዎችን ለመቋቋም በትብብር መሥራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል።
አዲሱ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ እና አወጋገድ አዋጅ 1383/2017 "ሁሉንም ዓይነት ፕላስቲኮች" ሙሉ በሙሉ አግዷል?
Feb 28, 2026 197
የኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን የፕላስቲክ ብክለትን በመቀነስ የአካባቢን ደህንነት ለማረጋገጥ ያለመውን አዲሱን የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ እና አወጋገድ አዋጅ 1383/2017 ወደ ትግበራ ማስገባቱ ይታወቃል። ይሁን እንጂ፣ የዚህን አዋጅ መውጣት ተከትሎ በማህበራዊ ሚዲያ አማራጮች ላይ ማህበረሰቡን የሚያሳስቱ መረጃዎች በስፋት እየተዘዋወሩ ይገኛሉ። በመሆኑም በማህበራዊ ሚዲያ ላይ በስፋት እየተሰራጩ ያሉትን ዋና ዋና አሳሳች መረጃዎች በመለየት፤ ከአዋጁ፣ ከኃላፊዎች ማብራሪያ እና ይፋዊ መግለጫዎች ጋር በማገናዘብ መረጃ ማጣራት ተደርጓል። የተሳሳተ መረጃ፡- "ማንኛውም ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ እንዳይመረት፣ እንዳይገባ እና እንዳይሸጥ ሙሉ በሙሉ ታግዷል" እውነታው፡- አዋጁ ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውሉ ፕላስቲኮችን በሙሉ አልከለከለም። በህጉ መሰረት ሙሉ በሙሉ የተከለከሉት ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውሉ "ስስ የፕላስቲክ ከረጢቶች (ፌስታል)" ብቻ ናቸው። የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 በግልጽ እንደሚያስቀምጠው፤ “ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ እንዲመረት፣ ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገባ ወይም ጥቅም ላይ እንዲውል መመሪያ ሊወስን ይችላል” ይላል። ይህም ማለት እንደየአስፈላጊነቱ የሚፈቀዱ ፕላስቲኮች አሉ። ይህንን ጉዳይ በተመለከተ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገጹ በሰጠው ማብራሪያ፤ የፕላስቲክ ማሸጊያ ማለት እቃዎችን ከብክለት ለመከላከል ወይንም ከሌላ ነገር ጋር እንዳይቀላቀል ለማድረግ የሚጠቅም መሆኑን ጠቅሶ፤ የምግብ፣ የባልትና ውጤቶች፣ የላውንደሪ አገልግሎት እና ሌሎች ምርቶችን ለማሸግ የሚውሉ የፕላስቲክ ማሸጊያዎች በአዋጁ የተፈቀዱ መሆናቸውን አረጋግጧል። የእነዚህ ማሸጊያዎች አወጋገድ በቀጣይ በሚወጡ መመሪያዎች የሚመራ ይሆናል። በተጨማሪም የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሌሊሴ ነሜ(ዶ/ር) ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት(ኢዜአ) በሰጡት ማብራሪያ፤ አዋጁ የፕላስቲክ ምርቶችን ሙሉ ለሙሉ የሚከለክል እንዳልሆነ በግልጽ አረጋግጠዋል። የተሳሳተ መረጃ፡- "የቁጥጥር ስራውን የሚያከናውነውና እርምጃ የሚወስደው የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ብቻ ነው" እውነታው፡- አዋጁን የማስፈጸም የበላይ ኃላፊነት የተሰጠው ለአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን እና ለክልል የአካባቢ ጥበቃ ቢሮዎች መሆኑ እውነት ቢሆንም፤ የቁጥጥር ስራው ግን በባለስልጣኑ ብቻ የሚከወን አይደለም። ህጉ ወደ መሬት ወርዶ ተግባራዊ ሲደረግ፣ በየዕለቱ ህገ-ወጥ ስስ የፕላስቲክ ከረጢቶችን በሚያመርቱ፣ በሚያስገቡ እና በሚጠቀሙ አካላት ላይ ክትትል የሚያደርጉት እና የቁጥጥር እርምጃ የሚወስዱት የፖሊስ እና የደንብ ማስከበር አካላት መሆናቸውን ዋና ዳይሬክተሯ አብራርተዋል። በመሆኑም ህዝቡ እና የንግዱ ማህበረሰብ የቁጥጥር ስራው በጸጥታና ደንብ አስከባሪ አካላት ጭምር የሚተገበር መሆኑን ሊገነዘቡት ይገባል። ህብረተሰቡ በማህበራዊ ሚዲያ የሚናፈሱ ያልተረጋገጡ አሳሳች መረጃዎችን ባለመቀበል የፕላስቲክ አጠቃቀምን በተመለከተ የሚወጡ መመሪያዎችን በቀጥታ ከባለስልጣን መስሪያ ቤቱ ይፋዊ ገጾች እና ከታማኝ ምንጮች ብቻ እንዲወስድ ይመከራል።
የፕላስቲክ ከረጢት ክልከላን ለማሳካት ህብረተሰቡ እያደረገ ያለው ተሳትፎ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል
Feb 27, 2026 210
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦ህብረተሰቡ የፕላስቲክ ከረጢቶች ላይ የተጣለውን ክልከላ ተግባራዊ ለማድረግ እያበረከተ ያለውን አስተዋፅኦ አጠናክሮ እንዲቀጥል የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ጥሪ አቀረቡ። ባለስልጣኑ ከአምራቾች ጋር በመሆን ተኪ ምርቶች በስፋት ለተጠቃሚ ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑንም ተናግረዋል። በሀዋሳ በፕላስቲክ ከረጢት ምትክ አማራጭ ምርቶችን የመጠቀም ልምድ እየዳበረ ነው የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ እና አወጋገድ አዋጅ 1383/2017 ከጥር 23 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የፕላስቲክ ከረጢት ማምረት፣ ወደ ሃገር ማስገባት፣ መሸጥና መጠቀም ላይ ሙሉ ክልከላ ማድረጉ ይታወቃል። የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት፤ አዋጁ በየጊዜው እየጨመረ የመጣውን የህዝብ ቁጥር፣ የከተሞች መስፋፋት እንዲሁም የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ስርዓት መዘርጋትን መነሻ በማድረግ የተዘጋጀ ነው። በለውጡ ዓመታት የተሰሩ የኮሪደርና ወንዝ ዳርቻ ልማት ስራዎች ፅዳት ማዕከል ያደረጉ እንዲሆኑ በማስቻል ንፁህና ፅዱ ለማድረግ አሁን ካለው ነባራዊ ሁኔታ ጋር የተጣጣመ አዋጅ ማዘጋጀት ማስፈለጉን ተናግረዋል። አዋጁ ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውሉ የፕላስቲክ ከረጢቶች(በተለምዶ ፌስታል የሚባሉት) ላይ ሙሉ በሙሉ ክልከላ ያደረገ አዋጅ መሆኑን አንስተዋል። አዋጁ የበርካታ ሀገራት ልምድን ከመቀመር ባለፈ የፕላስቲክ ከረጢቶች በጤና ላይ የሚያደርሱትን አሉታዊ ተፅዕኖ ታሳቢ በማድረግ መዘጋጀቱን ተናግረዋል። እነዚህ ፕላስቲክ ከረጢቶች ለካንሰር፣ ለአዕምሮ እድገት ውስንነት እና ለመተንፈሻ አካላት ህመሞች ምክንያት መሆናቸውን አንስተው፤ የአፈር ለምነትን፣ ውሃ አየር እና በእንስሳት ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያደርስ እንደሆነ እንዲሁም የምግብ ዋስትናንና ሉዓላዊነትንም እንደሚያደናቅፍ አመልክተዋል። የፕላስቲክ ከረጢት አጠቃቀም ልምድን ለመቀየር ለአንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውሉ ፕላስቲክ ከረጢቶች ሙሉ በሙሉ መከልከላቸውን አብራርተዋል። በአሁኑ ወቅትም በአብዛኞቹ የሀገሪቷ አካባቢዎች ሕጉ ተፈፃሚ መሆኑን ጠቅሰው፤ ጥብቅ የክትትል ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የአዋጁ ትግበራ የጊዜ ገደብ ተራዝሟል የሚል ሃሰተኛ መረጃ እየተሰራጨ እንደሚገኝ ጠቁመው፤ ህብረተሰቡ በዚህ የተሳሳተ መረጃ ሳይዘናጋ ለአዋጁ ተፈፃሚነት የበኩሉን ሚና መወጣቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል። ባለስልጣኑ ከአምራቾች ጋር በመሆን አማራጭ ምርቶች በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲቀርቡ እየሰራ መሆኑን አንስተው፤ በዚህም አብዛኛው ኢንዱስትሪዎች ምርቶችን በስፋት እያመረቱ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ አሁንም ምርትን በስፋትና በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ መስራት እንደሚጠይቅ ጨምረው አስታውቀዋል። በአካባቢ ላይ የሚደርሱ ብክለቶች ዙሪያ ጥቆማ የሚያደርሱበት እንዲሁም ቅሬታ የሚያቀርቡበት የዲጂታል ስርዓት ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር እየተዘረጋ መሆኑንም ጠቁመዋል።
በክልሉ በተያዘው የበጋ ወራት ከ64 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የአፈርና የውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት እየተከናወነ ነው
Feb 27, 2026 145
ጋምቤላ፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በተያዘው የበጋ ወራት ከ64 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የአፈርና የውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት በመከናወን ላይ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ። የቢሮ ኃላፊው አድሮው ቱት ለኢዜአ እንደገለጹት ምርታማነትን ለማሳድግ በበጋው ወራት የተጠናከረ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ። በክልሉ በሚገኙ ሶስቱም ዞኖች የአፈርና ውሃ ጥበቃ የተፋስ ልማት ስራዎች በተጠናከረ መልኩ እየተከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የተፋሰስ ልማት ስራዎች በክልሉ በሚገኙ 13 ወረዳዎች በተመረጡ 101 ተፋሰሶች በመደበኛና በፕሮጀክቶች ከ64ሺህ ሄክታር በላይ በሚሸፍን መሬት ላይ እየተከወነ መሆኑን ተናግረዋል። በተፋሰስ ልማት ስራው ከአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች በተጓዳኝ ባለፈው ክረምትና ከዚያ በፊት በአረንጓዴ አሻራ ልማት ለተተከሉ ችግኞች እንክብካቤ እየተደረገ እንደሆነም አክለዋል። በክልሉ በበጋው ወራት እየተካሄደ ያለውን የአፈርና ውሃ ጥበቃ የተፋሰስ ልማት ስራዎች በመጪው የአረንጓዴ አሻራ ልማት ስነ-ህይወት ለማላበስ በ66 የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች የማፍላት ስራ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። በመጪው ክረምት በሚከናወነው ለአረንጓዴ አሻራ ልማት መርሃ ግብር ከሚዘጋጁት ችግኞች መካከል ከ8 ነጥብ 2 ሚሊየን በላይ ከደንነት በተጨማሪ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው መሆናቸውን ኃላፊው ገልጸዋል።