አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
የበልግ አብቃይ የሆኑት የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ ይኖራቸዋል
Feb 9, 2026 58
አዳማ ፤ የካቲት 2/2018 (ኢዜአ)፦በአብዛኛው የበልግ አብቃይ የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛ እና ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚያገኙ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የበጋ ወቅት የአየር ፀባይ ትንበያ ግምገማና የበልግ ወቅት ትንበያ ይፋ ማድረጊያ መድረክ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በአዳማ ማካሄድ ጀምሯል። ኢንስቲትዩቱ በዚሁ መድረክ ላይ ይፋ እንዳደረገው የበልግ ወቅት የአየር ትንበያ በልግ ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት የሀገሪቱ አካባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚኖራቸው ጠቁሟል። በዚሁ መሰረት የቦረና እና ጉጂ ዞኖች ፣ሲዳማ እና ደቡብ ኢትዮጵያ ከመደበኛ በላይ ዝናብ ያገኛሉ። እንዳሁም የሶማሌ ክልል ደቡባዊ ክፍል እና የምእራብና ደቡብ ምእራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች ደግሞ መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚያገኙ ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል። በተጨማሪም በአሁኑ ወቅት እየተስተዋሉ ከሚገኙ የአየር ሁኔታ ክስተቶች ላይ በመነሳት በሰሜን ምእራብ በመካከለኛው፣ በምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይም መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ ይኖራል። በሌላ በኩል የቀኑ ከፍተኛ ሙቀት መጠን በሰሜን ምስራቅ፣ በሰሜን ምእራብ እና በደቡብ ምእራብ አካባቢዎች ላይ ከመደበኛ በላይ እንደሚሆን የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ። የበልግ ወቅት የዝናብ አጀማመር በደቡብ አጋማሽ አካባቢዎች ላይ ቀደም ብሎ የሚጀመር ሲሆን በአወጣጥ ረገድ ግን በተወሰኑ ቀናቶች ዘግይቶ ይወጣል ተብሏል። ይህን የዝናብ መጠንና ስርጭት በአግባቡ መጠቀምና በዚህ ወቅት የሚካሄደውን የግብርና እንቅስቃሴ እና ሌሎች ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ስራዎች ከባለሙያዎች ጋር በመመካከር ማከናወን ያስፈልጋል ተብሏል። በዘንድሮ የበልግ ወራት የዝናብ መጠንም ለግብርና ስራ አመቺ መሆኑ ተገልጿል።
ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁሉን አቀፍ የልማት ጉዞ ለማሳካት የአየር ንብረት መረጃዎችን በአግባቡ ስራ ላይ ማዋል ይገባል
Feb 9, 2026 61
አዳማ ፤ የካቲት 2/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁሉን አቀፍ የልማት ጉዞ ለማሳካት የአየር ንብረት መረጃዎችን በአግባቡ ስራ ላይ ማዋል እንደሚገባ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስገነዘበ። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የበጋ ወቅት የአየር ፀባይ ትንበያ ግምገማና የበልግ ወቅት ትንበያ ይፋ ማድረጊያ መድረክ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና የዘርፉ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በአዳማ ማካሄድ ጀምሯል። መድረኩን በንግግር የከፈቱት የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር አማካሪ አቶ ሞቱማ መቃሳ እንዳሉት፤ ኢንስቲትዩቱ የሚቲዎሮሎጂ መረጃዎችን አስተማማኝነትና ቅልጥፍና በማሳደግ ሁለንተናዊ ልማትን ለማሳካት በሚደረገው ጥረት የበኩሉን እየተወጣ ነው። የሚቲዎሮሎጂ መረጃዎቹ ለግብርና፣ ለውሃና ኢነርጂ፣ ለትራንስፖርት፣ ለአካባቢ ጥበቃና ለአደጋ አመራር፣ ለኢንሹራንስና ለኢንዱስትሪ ዘርፎች በሳይንሳዊ መንገድ ተተንትነው መቅረባቸውን ገልፀዋል። እነዚህ የትንበያና ቅድመ ማስጠንቀቂያ መረጃዎች ለውሳኔ ሰጪዎችና ለተጠቃሚው ማህበረሰብ ከፍተኛ እገዛ አድርገዋል ብለዋል። ኢትዮጵያ የጀመረችውን ሁሉን አቀፍ የልማት ጉዞን ለማሳካት የአየር ንብረት መረጃዎችን በአግባቡ ስራ ላይ ማዋል እንደሚገባም አማካሪው አሳስበዋል። የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፈጠነ ተሾመ በበኩላቸው፤ ኢንስቲትዩቱ ከአየር ሁኔታና ፀባይ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን መረጃዎች በየወቅቱ ለተጠቃሚዎች እየሰጠ ይገኛል ብለዋል። የበጋ፣ የበልግ፣ የክረምት የአየር ሁኔታና ፀባይ ትንበያዎችና የቅድመ ማስጠንቀቂያ አገልግሎቶች ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በማዋል ውጤት ማስገኘታቸውን አንስተዋል። የበጋ ወቅት የአየር ሁኔታ በጊዜና በቦታ ትንበያ ከክስተቶች ጋር በእጅጉ የተጣጣመ መሆኑን አስረድተዋል። በዛሬው መድረክም የአገራችን የበልግ ወቅት ዝናብ አዎንታዊና አሉታዊ ተፅእኖን ለመቋቋም ግንዛቤ ለመፍጠር ያለመ ነው ብለዋል። ህብረተሰቡም በኢንስቲትዩቱ የሚሰጠውን ትንበያ እና ቅድመ ማስጠንቀቂያ መረጃ በሚገባ በመከታተል ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባው ዋና ዳይሬክተሩ አሳስበዋል፡
በጋምቤላ ክልል የሙቀቱ መጠን እየጨመረ በመምጣቱ በመንግስት የስራ ስዓት ላይ ለውጥ ተደረገ
Feb 7, 2026 105
ጋምቤላ፤ ጥር 30 /2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል የሙቀቱ መጠን እየጨመረ በመምጣቱ የመንግስት የስራ ስዓት ላይ ለውጥ መደረጉን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድርና ካቢኔ ጉዳዮች ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የፅህፈት ቤቱ ኃላፊ አቶ ኡቶው ኡኮት፤ የሙቀቱ መጠን እየጨመረ በመምጣቱና ለስራ አስቸጋሪ በመሆኑ ከፊታችን ሰኞ የካቲት 2 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ የስራ ሰዓት ለውጥ መደረጉን ገልጸዋል። የተደረገው የሰዓት ለውጥ ለቀጣዮቹ ሶስት ወራት የሚቀጥል መሆኑን ጠቁመው በዚሁ መሰረት ሁሉም የመንግስት ተቋማት ተግባራዊ እንዲያደርጉ አሳስበዋል። በለውጡ መሰረትም ቀደም ሲል ከጧቱ 1:00 እስከ 6: 30 የነበረው ከ1:00 አስከ 5:30 እንዲሆን እንዲሁም ከስዓት በኋላ ከ9:00 እስከ 11:30 የነበረው 10:00 እስከ 12:30 ይሆናል ብለዋል። የስራ ስዓት ለውጡ ወይና ደጋ የአየር ንብር ያላቸውን የመንጌሽና የጎደሬ ወረዳዎችን እንደማይጨምር የገለጹት ኃላፊው የክልሉ የመንግስት ሰራተኛች በተጠቀሰው ጊዜ ወደ ቢሮ በመግባት ስራቸውን በትጋት እንዲያከናውኑ አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ ሜትዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የጋምቤላ ክልል የሜትሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል ተወካይ ነብዩ ፈረደ፤ በአሁኑ ወቅት የክልሉ አማካይ የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን 41.4 ድግሪ ሴልሸስ መሆኑን ጠቁመዋል። የሌሊቱ ዝቅተኛው የሙቀት መጠን ደግሞ 25 ነጥብ 6 ድግሪ ሴልሸስ መሆኑን ጠቁመው ባለፉት ወራት የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን በአማካኝ ከ35 ድግሪ ሴልሸስ የለሊቱ ደግሞ 22 ዲግሪ ሸልሰስ በታች እንደነበር አስታውሰዋል። በክልሉ የሞቃታማ ወራት የሚባሉት የካቲት፣ መጋቢትና ሚያዚያ ወራት ሲሆኑ በእነዚህ ወራት ውስጥ የቀኑ ከፍተኛ የሙቀት መጠን እስከ 45 ድግሪ ሴልሸስ የሚደርስበት ጊዜ እንዳለ መረጃዎች ይጠቁማሉ።
በምዕራብ ሐረርጌ ዞን አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የበጋ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው
Feb 7, 2026 98
ጭሮ፤ ጥር 30/2018 (ኢዜአ) ፡-በምዕራብ ሐረርጌ ዞን ከ700 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ የበጋ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። በዞኑ እየተከናወነ ያለውን የበጋ የአካባቢ ጥበቃ ስራ በተመለከተ ኢዜአ የሚመለከታቸውን የስራ ሃላፊዎችና የልማቱ ተሳታፊ አርሶ አደሮችን አነጋግሯል። በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሐረርጌ ዞን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ሃላፊ ሸረፍ አብደላ፤ በዞኑ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ በተለይም ተራቁተው የቆዩ ተራራማ አካባቢዎች እንዲያገግሙ ማድረጉን ገልጸዋል። በልማቱ የተገኘውን ውጤት ተከትሎ በበጋና ክረምት ጭምር የልማት ስራው ተጠናክሮ የቀጠለ መሆኑን አንስተዋል። በዚህም መሰረት በዘንድሮው የበጋ ወራት ከ700 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ በ455 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል። በልማቱ እስካሁን ከ109 ሺህ 700 ኪሎ ሜትር በላይ የአፈርና የድንጋይ እርከን ስራ በማከናወን የእቅዱን 95 በመቶ ማሳካት የተቻለ መሆኑን ተናግረዋል። ከልማቱ ተሳታፊ አርሶ አደሮች መካከል አርሶ አደር ጀማል አብዶ፣ ወይዘሮ ነስራ አብዱሬ እና አብነት ጉልላት፤ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራው አካባቢን ከመጠበቅም ባለፈ ለምርታማነት መጨመር ትርጉም ያለው በመሆኑ እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርታማነትን ከማሳደግም ባለፈ የጎርፍ አደጋን ለመከላከል ሁነኛ መፍትሄ መሆኑን ተናግረው አጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑን ገልጸዋል።
የተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርትና ምርታማነታችንን አሳድጎልናል- አርሶ አደሮች
Feb 6, 2026 94
ወላይታ ሶዶ ፤ ጥር 29/2018 (ኢዜአ)፡- የተፋሰስ ልማት ስራው የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርትና ምርታማነታቸውን ማሳደጉን በደቡብ ኢትዮጵያ እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች የሚገኙ አርሶ አደሮች ተናገሩ። በደቡብ ኢትዮጵያ እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልሎች ነዋሪ የሆኑ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንደገለጹት፤ እየተካሔደ ያለው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የመሬት ለምነትን በመመለስ ምርታማነት ለማሳደግ እያስቻለ ነው። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በወላይታ ዞን ኦፋ ወረዳ ነዋሪ አቶ ተስፋዬ ሜጊሶ እና ማርታ አዋሾ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ መጀመሩ በጎርፍ እየተጠረገ ይወሰድ የነበረውን ለም አፈር ጥቅም ለይ ለማዋል አስችሎናል ይላሉ። በአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው ሳቢያ የደረቁ ምንጮች ዳግም እንዲፈልቁ በማድረጉ የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲለሙ ማድረጉን አመልክተዋል። በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሀዲያ ዞን ምስራቅ ባድዋቾ ወረዳ ነዋሪ አርሶ አደር አበራሽ አቡቶ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሰራው የተራቆጡ አካባቢዎች ዳግም እንዲለሙ ማድረጉን ተናግረዋል ። በዚህም የተለያዩ የጓሮ አትክልት በማምረት ተጠቃሚ መሆን መቻላቸውን ጠቅሰው የተፋሰስ ልማት ስራን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ነው ያመለከቱት ። በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ ፋኖሴ መኮንን በበኩላቸው፤ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራው ምርታማነት በማሻሻል ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ ነው። ባለፉት ዓመታት በተሰራው ስራ እንደ ሀገር አደጋ ላይ ከነበሩ 54 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት ውስጥ 33 ነጥብ 6 ሚሊዮን በላይ የሚሆነው ዳግም እንዲያገግም ለማድረግ ተችሏል ነው ያሉት።። በተለይም የአፈር ለምነትን በመጨመር፣ የደረቁ ምንጮች ዳግም እንዲፈልቁ በማድረግ እና ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ጉልህ ሚና መጫወቱንም ነው ያነሱት። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራው እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተደረገ ያለውን ጥረት ለማሳካት የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ጠቅሰዋል። በዘንድሮው ዓመትም 25 ሚሊዮን የህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በ23 ሺህ ተፋሰሶች ላይ 4 ነጥብ 6 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ለማልማት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ገልፀዋል። ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያለው የተፋሰስ ልማት ስራ ላይ እየታየ ያለው የህብረተሰብ የተሳትፎ ባህል መጠናከር እንደሚገባውም አሳስበዋል።
የሐረማያ ሐይቅ የቱሪስት መዳረሻነት የማበልጸግ ስራ በተቀናጀ መንገድ በመከናወን ላይ ይገኛል
Feb 2, 2026 178
ሐረማያ ፤ጥር 25/2018 (ኢዜአ) ፡-የሐረማያ ሐይቅን የቱሪስት መዳረሻነቱን የማበልጸግ ስራ በተቀናጀ መልኩ እየተካሔደ መሆኑን የኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ገለጸ። በማያ ከተማ አስተዳደር ከሚገኙት የቱሪስት መዳረሻዎች መካከል የሐረማያ ሃይቅ እንዱ ነው። ለበርካታ ዓመታት ደርቆ የነበረው ሐይቁ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና የአረንጓዴ አሻራ ስራዎች ትኩረት ተደርጎ በመከናወናቸው ወደ ቀድሞው ይዞታው መመለስ ችሏል። የከተማ አስተዳደሩ እና የአካባቢው ማህበረሰብ ሃይቁን እያለማውና እየተንከባከበው በመሆኑም የጎብኚዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን የኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ወይዘሮ ጀሚላ ሲምቢሩ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ሐይቁ ከመዝናኛነቱ ባለፈ ለወጣቶች የስራ እድል እየፈጠረ የሚገኝ ሲሆን በዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የማጎልበት ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም አረጋግጠዋል። አካባቢው ትልልቅ እሴቶችና ጸጋዎች የሚገኙበትና በኪነ ጥበቡም ዘርፍ ስመ-ጥር አርቲስቶች የፈለቁበት መሆኑንም ይገልፃሉ። የአካባቢውን ባህል፣ ኪነ ጥበቡብና ቱሪዝሙ ዘርፉን እንደ አንድ ጸጋ በመጠቀምና ከቱሪዝም ጋር በማሰናሰል የዘርፉን ኢኮኖሚ ማሳደግና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል። የማያ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ኢፍራህ ወዚር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በአፈርና ውሃ ጥበቃ እና በአረጓዴ አሻራ ስራ የተመለሰውን የሐረማያ ሃይቅ አጠቃቀምን የማስተካከል፣ የመጠበቅና የመንከባከብ ስራ እየተከናወነ ይገኛል። ሐይቁ ወደ ቀድሞ ቦታው መመለሱ ለጎብኚዎች እርካታን ከማጎናጸፉ ባለፈ ለአካባቢው ነዋሪዎችና ለወጣቶች የገቢ ምንጭ እየሆነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የሐረማያ ሐይቅ በተደረገለት እንክብካቤ ውብና ማራኪ የቱሪስት ቀልብ የሚስብ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፤ ለወጣቶችም የገቢ ምንጭ ማግኛ ሆኗል ያለው ደግሞ በኦሮሚያ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ የቱሪዝም ባለሙያ ኦሊያድ በሪሶ ናቸው። በአካባቢው ባለሀብቶችን በመጋበዝ ሎጆችና ሪዞርቶች በማስፋፋት የተሻሉ ስራዎችን መስራት እንደሚቻልም ነው አቶ ኦሊያድ አስተያየታቸውን የሰጡት። በሐረማያ ሐይቅ ላይ የጀልባ አገልግሎት የሚሰጠው ወጣት ሙርቲ አህመድ፤ጎብኚዎችን በጀልባ ከማስጎብኘት ስራ በተጨማሪ በአሳ ልማት ስራም መሰማራቱን ይገልፃል።
በአማራ ክልል የበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች ምርታማነት እንዲጎለብት አግዘዋል
Feb 2, 2026 197
ባህር ዳር፤ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፡- አማራ ክልል የበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርታማነት እንዲጎለብት እገዛ ማድረጋቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማት፤ ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ለኢዜአ እንዳሉት በክልሉ የበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች የአፈር ለምነትን በመጨመር ምርታማነት እንዲያድግ አግዘዋል። ስራውን በማስቀጠልም በያዝነው የበጋ ወራት በተለዩ ዘጠኝ ሺህ 206 ተፋሰሶች በ456 ሺህ 411 ሄክታር መሬት ላይ የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ለማከናወን ግብ ተይዞ ወደ ተግባር ተገብቷል። እስካሁን በተደረገ ጥረትም የዕቅዱን 37 በመቶ ማከናወን እንደተቻለ ጠቅሰው፤ በዚህም ከ3 ነጥብ 8 ሚሊዮን በላይ አርሶ አደሮች መሳተፋቸውን ገልፀዋል። ከዚሁ በተጓዳኝም ለመጪው ክረምት ወራት የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ የሚሆን ቦታ የመለየትና ለተከላ የሚውል ከ አንድ ነጥብ 7 ቢሊዮን በላይ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን አንስተዋል። በተቀናጀ የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ ላይ ከተሰማሩ አርሶ አደሮች መካከል በደቡብ ጎንደር ዞን የፋርጣ ወረዳ አርሶ አደር ዓለሙ መንጌ በበኩላቸው፤ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ከህልውና ጋር የተያያዘ መሆኑን በመረዳት ተግባሩን በማጠናከር በየዓመቱ በራሳቸው ተነሳሽነት እያከናወኑ መሆናችውን አንስተዋል። ዘንድሮም በቀበሌያቸው በተጀመረው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ ላይ በንቃት በመሳተፍ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት በቀበሌያቸው ያከናወኑት የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ የመሬቱን ለምነት በመመለስ ለምርታማነት ማደግ አስተዋጽኦ እንዳበረከተላቸው የገለፁት ደግሞ ሌላኛው የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ካሳሁን መንግስት ናቸው። ቀደም ሲል የተሰራው የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራ ግማሽ ሄክታር የእርሻ ማሳቸውን ለምነት በመመለሱ እስከ አምስት ኩንታል ተጨማሪ ምርት እንዲያገኙ ማስቻሉን ገልፀዋል። የልማት ስራው ተጠቃሚነታቸውን በተጨባጭ እያሳደገ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ በበጋ ወራት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራ ላይ እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ባለፉት ዓመታት የተከናወነ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራም የደን ሽፋንን ከማሳደግ ባሻገር በግብርና ምርታማነት ላይ ተጨባጭ ለውጥ ማስመዝገብ እንዳስቻለም ተመላክቷል።
የአረንጓዴ አሻራ፣ የተፋሰስ ልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማቶች የውሃ አዘል መሬቶችን ከመጠበቅ አኳያ ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ ነው
Feb 2, 2026 175
አዲስ አበባ፤ ጥር 25/2018 (ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ፣ የተፋሰስ ልማት እና የወንዝ ዳርቻ ልማቶች የውሃ አዘል መሬቶችን ከመጠበቅ አኳያ ተጨባጭ ውጤት እያስገኙ መሆኑን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ፡፡ ባለስልጣኑ የዘንድሮውን የዓለም የውሃ አዘል መሬቶች ቀን "የውሃ አዘል መሬት እና ሀገር በቀል እውቀት፤ የባህል ቅርሳችንን እናክብር" በሚል መሪ ቃል እያከበረ ይገኛል። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ የተለያዩ የውሃ አዘል መሬቶች እና የብዝሃ ህይወት ባለቤት ናት። እነዚህ ተፈጥሯዊ ጸጋዎች ተጠብቀው ለትውልድ እንዲሸጋገሩም ሀገር በቀል እውቀት እና ባህላዊ የጥበቃ ስልቶች ከፍተኛ ሚና ሲጫወቱ መቆየታቸውን ገልጸዋል። የውሃ አዘል መሬቶች ከፍተኛ ጥቅም እያስገኙ መሆኑን ጠቁመው የተበከለ ውሃን በተፈጥሯዊ መንገድ ማጣራት፣ የጎርፍ አደጋን መከላከል እና የአፈር እርጥበትን መጠበቅ እንዲሁም የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም እና የአካባቢን ሙቀት መቀነስን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ በእነዚህ ወሳኝ የተፈጥሮ ሃብቶች ላይ የሚደርሱ ተግዳሮቶችን ለመፍታት ዘመናዊውን ሳይንሳዊ እውቀት ከሀገር በቀል ጥበብ ጋር አቀናጅቶ መተግበር እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተተገበሩ ያሉ የአረንጓዴ አሻራ እና የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክቶች ለውሃ አዘል መሬቶች ደህንነት ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን አረጋግጠዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአካባቢ ጥበቃና ደን ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ግዛቴ ግጄ፤ በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ውሃ አዘል መሬቶችን የመለየትና ተገቢውን ጥበቃ የማድረግ ተግባር በትኩረት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የአማራ ክልል የአካባቢ ጥበቃና ደን ባለሥልጣን ምክትል ዳይሬክተር አቶ በልስቲ ፈጠነ በበኩላቸው፤ በክልሉ የሚገኙ የውሃ አዘል ስፍራዎችን በዘላቂነት ለማልማት ዘመናዊ ሳይንሳዊ ዕውቀቶችን ከባህላዊ ጥበቃ ዘዴዎች ጋር በማቀናጀት እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ማህበረሰቡ ስለ እርጥብ መሬቶች ፋይዳ ያለውን ግንዛቤ እንዲያሳድግና ከሀብቱ በሥርዓት ተጠቃሚ እንዲሆን ሰፊ የትምህርትና የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የኦሮሚያ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የብዝሃ ሕይወት ጥበቃ ዳይሬክተር አቶ ብርሃኑ ኢዳቲ ጠቁመዋል።
በዞኑ አርብቶ አደሩን በማሳተፍ ከ33 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው
Jan 31, 2026 192
ጂንካ፤ ጥር 23/2018(ኢዜአ):- በደቡብ ኦሞ ዞን አርብቶ አደሩን በማሳተፍ ከ33 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የአፈርና ውሃ ጥበቃና የግጦሽ ሳር መከለል ስራ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። የመምሪያው ኃላፊ ምንላርገው አዲሱ፣ በዞኑ በተጀመረው የተፋሰስ ንቅናቄ ከ16 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት 50 ንዑስ ተፋሰሶች የማልማት ስራ እንዲሁም በአርብቶ አደርና በዝቅተኛ አካባቢዎች ደግሞ ከ17 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የግጦሽ ሳር መከለል ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ በዞኑ ከ33 ሺህ ሄክታር መሬት የተፋሰስና የግጦሽ ሳር መከለል ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፥ የተፋሰስ ልማቱ በተከናወነባቸው ስፍራዎች ከ11 ሚሊየን በላይ ሀገር በቀል ችግኞች ተከላ ይከናወናል ነው ያሉት። በዘንድሮው ዓመት የተፋሰስ ልማት በሳይንሳዊ ጥናት የተደገፈ ስነ-አካላዊና ስነ-ህይወታዊ ስራዎች እንደሚከናወኑም ጠቁመዋል። ልማቱ የተከናወነባቸው አካባቢዎችን ከሰውና ከእንሰሳት ንክኪ ነፃ በማድረግ የተተከሉ ችግኞችን የመንከባከብ ስራ እንደሚሰራም ገልጸዋል። በዞኑ ሐመር ወረዳ እየተከናወነ ባለው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የተሳተፉት ወይዘሮ አልጎ በሌ፥ በአካባቢው የቡስካ ጥብቅ ደን እንደሚገኝ ተናግረዋል። ቀደም ሲል ደኑ በሰውና በእንስሳት ጉዳት ይደርስበት እንደነበር አስታውሰው አሁን ላይ ደኑን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ነፃ በማድረግ የመጠበቅ ስራ ላይ እየተሳተፉ እንደሚገኙ ጠቁመዋል። በአካባቢያችን የተፋሰስ ልማት ከተጀመረ ወዲህ አካባቢው ለእርሻ ተስማሚ መሆን ጀምሯል ያሉት አቶ አስ ኦቶሎ ለእንስሳት የሚሆን በቂ የግጦሽ ሳር የምናገኝበት ዕድልንም እየፈጠረ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠት ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች ነው
Jan 29, 2026 152
አርባምንጭ፤ ጥር 21/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ዓለምአቀፍ ተግዳሮት ለሆነው አየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠት ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች መሆኗን የፕላንና ልማት ሚኒስቴር አስገነዘበ። የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአካባቢ አየር ንብረት ለውጥ ዘርፍና የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን የስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ እየተካሄደ ነው። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴዔታ ስዩም መኮንን በዚሁ ወቅት፤ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ፣ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ግንባታ እንዲሁም የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ላይ በትኩረት እየሠራች ነው ብለዋል። ዓለምአቀፍ ተግዳሮት ለሆነው የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ለመስጠትም ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች መሆኗን አስገንዝበዋል። የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብርን ጨምሮ በሀገር በቀል ስልቶች ለአየር ንብረት ለውጥ እየተሰጠ ባለው ምላሽም ተጨባጭ ውጤት መምጣቱን አረጋግጠዋል። የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬነሽ መኩሪያ እንዳሉት፤ ዜጎች ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ የመኖር መብታቸውን ለማረጋገጥ የጽዱና አረንጓዴ ልማት ሥራዎች ተሠርተዋል። የከተሞች ኮሪደር ልማትን ጨምሮ የጽዱ ኢትዮጵያ፣ የወንዝ ዳርቻና የአረንጓዴ ዐሻራ ኢኒሼቲቮች ለውጤቱ መገኘት ጉልህ ድርሻ አንዳላቸው አመልክተዋል። ባለፉት ስድስት ወራት የአካባቢ ቁጥጥር ሥርዓትን ለማጠናከር የወጡ ሕጎችና መመሪያዎች ተፈጻሚነት ላይ ተከታታይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች መሠራታቸውንም አንስተዋል። በዚህም የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ፣ በአካባቢ ማኅበራዊ ተጽዕኖ ግምገማ እንዲሁም በብዝኃ ሕይወት ጥበቃ ላይ የተሻለ ውጤት መምጣቱን አንስተዋል።
በተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር ለምነት በመጨመሩ የአርሶአደሮች ምርታማነት አድጓል
Jan 28, 2026 230
ወላይታ ሶዶ ፤ ጥር 20/2018 (ኢዜአ)፡- በተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር ለምነት በመጨመሩ ምርታማነታቸው ማደጉን በወላይታ ዞን የኦፋ ወረዳ አርሶ አደሮች ተናገሩ። "እመርታ በተቀናጀ ተፋሰስ ለብልፅግናችን!" በሚል መሪ ሃሳብ የ2018 ዓ.ም ዞናዊ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት የማስጀመሪያ መርሃ ግብር በዞኑ ኦፋ ወረዳ ቡሻ ቀበሌ ጋዬ ንዑስ ተፋሰስ ላይ ተካሄዷል። በወቅቱም ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ አርሶ አደሮች እንዳሉት፤ በተፋሰስ ልማት ስራው የአፈር ለምነት በመጨመሩ ምርታማነታቸው አድጓል። ከአርሶ አደሮቹ መካከል አርሶ አደር በቀለ ቶጋ፤ ለበርካታ ዓመታት በተፋሰስ ልማት ስራ ላይ ሲሳተፉ መቆየታቸውን ገልፀው በአካባቢው የልማት ስራው ከመከናወኑ በፊት በነበረው የአፈር በጎርፍ መሸርሸር ሳቢያ መሬቱ ተራቁቶ እንደነበር ገልጸዋል። ሆኖም ባለፉት ዓመታት የተከናወነው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የአፈር ለምነት እንዲጨምርና ምንጮች እንዲፈልቁ በማድረጉ በስራው በዘላቂነት እንድንሳተፍ መነሳሳትን ፈጥሮልናል ብለዋል። የአየር መዛባትና የአካባቢ መራቆት ከሁሉም በላይ አካል ጉዳተኞች ላይ የሚያደርሰው አሉታዊ ተጽዕኖ የከፋ በመሆኑ አካል ጉዳተኝነት ሳይበግረኝ የሚጠበቅብኝን እየተወጣሁ እገኛለሁ ያሉት ደግሞ አርሶ አደር መሰለ መንገሻ ናቸው። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው ከዚህ ቀደም የተራቆቱ አካባቢዎች አገግመው ምርት እንዲሰጡ ከማድረጉም ባሻገር ለኑሮ ምቹ አካባቢን ፈጥሮልናል ብለዋል። የአፈር ለምነት በጨመረባቸው እና ምንጭ በፈለቀባቸው አካባቢዎች የተለያዩ የጓሮ አትክልቶችን በማምረት ተጠቃሚ መሆን መጀመራቸውን ተናግረዋል። የኦፋ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አዲሱ ወርቁ በበኩላቸው፤የተቀናጀ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ለዘላቂ የግብርና ልማት ወሳኝ በመሆኑ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። በወረዳው በዘንድሮ የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ሥራ ከ31 ሺህ በላይ ህብረተሰብ ክፍሎችን በማሳተፍ በ20 ንዑስ ተፋሰሶች ከ2 ሺህ 400 ሄክታር በላይ መሬት ለማልማት መታቀዱን ገልጸዋል። በዞኑ ባህል ሆኖ የቀጠለው የተፋሰስ ልማት ስራ በስነ-አፈር እና በስነ-አካላዊ ስራዎች የተራቆቱ አካባቢዎች በማገገማቸው ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱን የተናገሩት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ ዘማች ሶርሳ (ዶ/ር) ናቸው። ይህንን ውጤት ለማስቀጠል በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው በዘንድሮ የተፋሰስ ልማት ስራ በዞን ደረጃ በ315 ተፋሰሶች ከ46 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ለመሸፈን ታቅዶ ስራ መጀመሩን ነው የገለጹት። በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የወላይታ ዞን ብልጽግና ፖርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አማረ አቦታ (ዶ/ር)፤ በዞኑ የተፋሰስ ልማት ስራ ከተጀመረ ወዲህ የተራቆተ መሬት በማገገሙ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ መቻሉን ገልጸዋል። የግብርና ምርታማነትን ለማሻሻል የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን በተገቢው ማስረጽ እንደሚገባ ገልጸው ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ስራ በመሳተፍ ኃላፊነቱን እንዲወጣም አሳስበዋል።
በመጪው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ችግኞች ዝግጅት ተጠናክሮ ቀጥሏል
Jan 27, 2026 164
ጊምቢ፤ ጥር 19/2018(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ወለጋ ዞን በመጪው ክረምት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ዝግጅት ተጠናክሮ መቀጠሉን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት ገለጸ። በኦሮሚያ ክልል የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር አካል የሆነው የችግኝ ዝግጅት ስራ በተለያዩ ዞኖች በሰፊው እየተካሄደ ይገኛል። በምዕራብ ወለጋ ዞንም ከበጋ ወራት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ ጎን ለጎን የችግኝ ዝግጅት በሰፊው እየተከናወነ መሆኑ ተገልጿል። በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ፍቅሩ ብርሃኑ እንደገለጹት፤ በመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ ነው። እየተዘጋጁ ከሚገኙ ችግኞች መካከል አብዛኛዎቹ ለምግብነት የሚውሉ የአትክልትና ፍራፍሬ ችግኞች ሲሆኑ ለደን እና ለውበት አገልግሎት የሚውሉ ችግኞችም እየተዘጋጁ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም የአቮካዶ፣ ፓፓያ፣ ማንጎ፣ ሙዝና የአናናስ ችግኞች በስፋት እየተዘጋጁ መሆኑን አንስተው ችግኞቹ የሚተከሉት በ66 ሺህ 827 ሄክታር መሬት ላይ መሆኑንም ገልጸዋል። የችግኝ ዝግጅቱ እየተደረገ ያለው ከ2 ሺህ 900 በላይ በሆኑ የመንግስትና የግል ችግኝ ማፊያ ጣቢያዎች መሆኑን ጠቅሰው በችግኝ ዝግጅት ስራው ከ3 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸዋል። በአጠቃላይ በዞኑ ከ3 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ለተከላ እየተዘጋጁ መሆኑን አስረድተዋል።
የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ህብረተሰቡን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ማድረግ አስችሏል
Jan 27, 2026 330
አሶሳ፤ ጥር 19/2018 (ኢዜአ)፡- የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የደን ሽፋንን ከማሳደግ ባለፈ ህብረተሰቡን በኢኮኖሚ ተጠቃሚ ማድረግ ማስቻሉን የኢትዮጵያ የደን ልማት አስታወቀ። በኢትዮጵያ እየተከናወነ የሚገኘው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር በርካታ የኢኮኖሚ ጠቀሜታ ያላቸው እንዲሁም የደን ሽፋንን የሚያሳድጉ ችግኞች እንዲተከሉ አድርጓል። በተለይም የመሬት መራቆት እና የአየር ንብረት ለውጥ በስነ ምህዳር ላይ አሉታዊ ተዕፅኖ እንዳያመጣ የኢትዮጵያ መንግስት የወሰደው እርምጃ ለሌሎች ሀገራትም ምሳሌ መሆን ችሏል። የኢትዮጵያ ደን ልማት ዋና ዳይሬክተር ከበደ ይማም ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ በኢትዮጵያ ከለውጡ በፊት በየዓመቱ እስከ 92 ሺህ ሄክታር ደን እንደሚወድም አስታውሰዋል። መንግስት በጀመረው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር በየዓመቱ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል የደን ሽፋንን በፈረንጆቹ አቆጣጠር 2030 ላይ 30 በመቶ ለማድረስ እየተሰራ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ የደን ሽፋን በአሁኑ ሰዓት 23 በመቶ ላይ ያለ መሆኑን ጠቅሰው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ችግኞችን ከመትከል ባለፈ ህብረተሰቡ የደን ምርት አስፈላጊነትን እንዲገነዘብ አድርጓል ነው ያሉት። የኢትዮጵያ የደን ሽፋን ለቀጠናው ሀገራት የውሃ ሀብት እንዲጨምር እና የአየር ንብረት ለውጥ እንዲስተካከል በማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ጠቁመዋል። የአሁኑ የበጋ ወቅት ደግሞ በአንዳንድ የሀገሪቱ የተፈጥሮ ደኖች አካባቢ የሰደድ እሳት እንዳይነሳ ቀድመው መከላከል እንዲችሉ በሳተላይት የታገዘ የቅድመ ማስጠንቀቂያ እየተሰጠ እንደሆነ ገልጸዋል። ህብረተሰቡ ለደን ልማት የሰጠው ትኩረት እና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ጠቅሰው በተሰራው ስራ በየዓመቱ የሚወድመው ደን እየቀነሰ መምጣቱን ተናግረዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልን ጨምሮ በሀገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች በስፋት የሚገኘው የቀርከሃ ሀብትን በአግባቡ ለመጠቀም የሚያስችል እና የቀርከሃ ችግኞችን በመትከል ህብረተሰቡ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተደረገ ነው ብለዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ1 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር በላይ የቀርከሃ ደን እንደሚገኝ ጠቁመው፣ የቀርከሃ ደን ሽፋንን ለማሳደግ በየዓመቱ ከ50 ሚሊዮን በላይ ችግኝ እየተተከለ መሆኑን አብራርተዋል።
በወረዳው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራው በግብርናው ዘርፍ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳደገ ነው
Jan 26, 2026 171
አምቦ፤ ጥር 18/2018 (ኢዜአ)፡- በምዕራብ ሸዋ ዞን ቶኬ ኩታዬ ወረዳ ባለፉት ዓመታት በተከታታይ ሲከናወን የቆየው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ስራ በግብርና ዘርፍ የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያሳደገ መምጣቱ ተገለጸ፡፡ ኢዜአ ያነጋገራቸው በዞኑ የቶኬ ኩታዬ ወረዳ አርሶ አደሮች ባለፉት ዓመታት ባከናወኑት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ በርካታ ጥቅም እያገኙ መሆኑን ገልጸዋል። የተቀናጀ የአፈርና የውሀ ጥበቃ ስራው ቀደም ሲል በጎርፍ የሚጠረገውን ለም አፈር በማስቀረት ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጉን ተናግረዋል፡፡ በወረዳው የዋጅራ ቀበሌ ነዋሪው ባይሳ ሚደቅሳ እንዳሉት ባለፉት ዓመታት ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር የሰሩት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ የግብርና ልማት ስራዎቹን ውጤታማ አድርጓል። ባለፉት ዓመታት ባከናወኑት ስራ በጎርፍ ተጠርጎ ተራቁቶ የነበረው መሬት ማገገም በመቻሉ ከአንድ ሄክታር መሬት አራት ኩንታል ምርት ማግኘት መቻላቸውን ተናግረዋል። ሌላው በቶኬ ኩታዬ ወረዳ የማሩፍ ቀበሌ አርሶ አደር አቦምሳ ፊጣ፤ በአካባቢያቸው በተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ስራዎች ደርቀው የነበሩ ምንጮች ጭምር መመለስ መጀመራቸውን ገልጸዋል። በዚህም የተፋሰስ ልማት የተከናወነበት መሬት በማገገሙ የዝናብ ወቅትን ብቻ ጠብቀው ከማምረት ወጥተው በአመት ሁለቴ በማምረት ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል። ተፋሰስ ልማት በተሰራባቸው አካባቢዎች ከሰብል ምርት ከሚያገኙት ገቢ በተጨማሪ ለእንስሳት መኖ ልማትም እየጠቀማቸው መሆኑን ጠቁመዋል። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራውን ውጤታማ ለማድረግ ከግብርና ባለሙያዎች ስልጠና መውሰዳቸውን የጠቀሱት ደግሞ በወረዳው የዋጅራ ቀበሌ አርሶ አደር ጋዲሳ ደንደና ናቸው፡፡ የቶኬ ኩታዬ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሃብት ቡድን መሪ ወይዘሮ ባዳዲ ዱጋሳ እንደገለጹት፤ ባለፉት ዓመታት በወረዳው በተሰሩ የተፋሰስ ልማት ስራዎች የገጸ ምድርና የከርስ ምድር ውሃ በመጎልበቱ የአርሶአደሩ ምርትና ምርታማነት ጨምሯል፡፡ ስራውን በዘንድሮው ዓመትም በማስቀጠል ከ23 ሺህ በላይ ሰዎችን ክፍሎችን በማሳተፍ 2 ሺህ 234 ሄክታር መሬት የማልማት ስራዎች መጀመራቸውን ተናግረዋል ፡፡ የምዕራብ ሸዋ ዞን ግብርና ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብዲሳ ሀይሉ በበኩላቸው፤ በዘንድሮ የበጋ ወራት ከ 273 ሺህ ሄክታር መሬት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች በሁሉም ወረዳዎች መጀመሩን ገልጸዋል ። ባለፈው ዓመታት በዞኑ በተሰሩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችም የአፈር ለምነትን መጠበቅና የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል የአርሶአደሩን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ አልፎ ኢኮኖሚ ተጠቃሚነታቸው ማረጋገጥ መቻሉን ጠቁመዋል፡፡
ወቅታዊ የአየር ንብረት መረጃ የማይበገር የማህበረሰብ አቅም ለመገንባት ቁልፍ ሚና አለው - ኢጋድ
Jan 26, 2026 219
አዲስ አበባ፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፦ ወቅታዊ የአየር ንብረት መረጃ የማይበገር ማህበረሰብ ለመገንባትና ለዘላቂ ልማት ጉልህ ሚና እንዳለው የምስራቅ አፍሪካ የልማት በየነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) አመለከተ። ኢጋድ የአየር ንብረት ትንበያና ትግበራ ማዕከል ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 72ኛው የአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ምልከታ መድረክ(GHACOF 72) ዛሬ በኬንያ ናይሮቢ ተጀምሯል። “የአየር ንብረት መረጃ እና አገልግሎቶች መጠናከር፤ በታላቁ የአፍሪካ ቀንድ የአይበገሬ ማህበረሰቦችን ለመገንባትና ዘላቂ ልማት ያለው ሚና” የስብሰባው መሪ ሀሳብ ነው። የኢጋድ አባል ሀገራት ባለስልጣናት፣ በቀጣናው የሚገኙ የአየር ንብረት ትንበያ ተቋማት፣ የአየር ንብረት ሳይንቲስቶች፣ የልማት አጋሮች፣ የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል። የአየር ንብረት መረጃ እና አገልግሎቶችን ማጠናከርና ማስፋት፣ ወቅታዊ መረጃዎችን ለውሳኔ መጠቀም፣ አይበገሬነትን መገንባትና ዘላቂ ልማትን ማረጋገጥ የመድረኩ አበይት ትኩረቶች ናቸው። በተለይም የአየር ትንበያዎች፣ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓቶች፣ ቴክኖሎጂዎች መጠቀምና ወቅትን ጠብቀው የሚወጡ መረጃዎች ድርቅና ጎርፍን ጨምሮ ሌሎች አደጋዎችን አስቀድሞ በመካለከልና የምላሽ አቅምን በማጠናከር ረገድ ያላቸውን ሚና አስመልክቶ ምክክር ይደረጋል። የአየር ንብረት መረጃን የምግብ ዋስትና፣ የኢኮኖሚ መረጋጋትትና ዘላቂ አካባቢ ጥበቃን ጨምሮ ከሌሎች የልማት ግቦች ጋር በማስተሳሰር የተሻለ ውጤት ማግኘት በሚቻልበት ሁኔታ ላይም ይወያያሉ። በስብሰባው የኢጋድ የአየር ንብረት ትንበያና ትግበራ ማዕከል ከእ.አ.አ ማርች እስከ ሜይ የዝናብ ወቅት ያለውን ቀጣናዊ የአየር ትንበያ መረጃ ይፋ ያደርጋል። ትንበያው ለግብርና፣ ውሃ፣ ጤና እና ለአደጋ ዝግጁነት ያለው ፋይዳ ውይይት እንደሚደረግበት ኢዜአ ከማዕከሉ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የዘርፉ ባለሙያዎች እና ባለድርሻ አካላት የአየር ንብረት ለውጥ ስጋቶችን መቀነስ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ለፖሊሲ አውጪዎችና የልማት አጋሮች ምክረ ሀሳቦችንና ስትራቴጂካዊ ሰነዶችን ያቀርባሉ። ኢጋድ በአየር ንብረት ትንበያና ትግበራ ማዕከሉ አማካኝነት የአየር ትንበያ መረጃዎችን በየጊዜው በማውጣትና የአባል ሀገራትን የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት ማጠናከር የሚያስችሉ ድጋፎችን እያደረገ እንደሚገኝ አመልክቷል። የሞባይል ስልኮች እና ሌሎች የዲጂታል አማራጮችን በመጠቀም ለአርሶ እና አርብቶ አደሮች የግብርናና አየር ንብረት የማማከር አገልግሎቶች ኢኒሼቲቭ(DACAS ) እየተገበረ እንደሚገኝም ገልጿል። ቀጣናዊ ተቋሙ ከእ.አ.አ 2023 አንስቶ ለሰባት ዓመታት የሚቆይ ቀጣናዊ የአየር ንብረት ለውጥ መቋቋሚያ ስትራቴጂን በመቅረጽ አባል ሀገራት እንዲተገብሩ አድርጓል። ድንበር ተሻጋሪ የአይበገሬነት አቅምን የሚገነቡ ፕሮግራሞች፣ ጤና እና ምግብን ጨምሮ ዘርፍ ተኮር ትብብርን ማጠናከር፣ አቅም ግንባታ፣ ጥናትና ምርምር እንዲሁም የእውቀት ሽግግር መድረኮችን ማዘጋጀት በአየር ንብረት አገልግሎት እና አይበገሬነት እያከናወናቸው ካሉ ስራዎች መካከል ተጠቃሽ ናቸው። የአፍሪካ ቀንድ ድርቅ እና ጎርፍን ጨምሮ ለሌሎች ተፈጥሯዊ አደጋዎች ተጋላጭ ቀጣና ሲሆን ይህም በምግብ ዋስትና፣ የውሃ አቅርቦት፣ ጤና፣ መሰረተ ልማት እና ኢኮኖሚ ላይ ተጽእኖ እንዲያሳድር ምክንያት ሆኗል። ዛሬ የተጀመረው ቀጣናዊ ውይይት የአየር ንብረት ሳይንስን ለአስቀድሞ መከላከልና ምላሽ መጠቀም የሚቻልበትን ሁኔታ በማሳለጥ ረገድ የበኩሉን ሚና እንደሚወጣም ድርጅቱ አመልክቷል። በቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት የዜጎችን ህይወትና የአኗኗር ሁኔታ ለመጠበቅ እንዲሁም ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ ጉዳቶች የማይገበር አቅም መገንባትና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ወሳኝ ሚና እንዳለው ተገልጿል። 72ኛው የአፍሪካ ቀንድ የአየር ንብረት ምልከታ መድረክ (GHACOF 72) እስከ ነገ ይቆያል።
ባህል እየሆነ የመጣው የተፋሰስ ልማት የቡና ምርታማነትን እያሳደገ ነው
Jan 26, 2026 148
ዲላ ፤ ጥር 18/2018(ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን ባህል እየሆነ የመጣው የተፋሰስ ልማት የቡና ምርታማነትን እያሳደገ መሆኑን የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) ገለጹ። በዞኑ የ2018 ዓ.ም የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ በገደብ ወረዳ ሐርሙፎ ቀበሌ አዳሜ ሃገሌ ተፋሰስ ተጀምሯል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ የተፋሰስ ልማት የጌዴኦ ባህላዊ መልክዓ ምድር ተጠብቆ እንዲቆይ እገዛ እያደረገ ነው ብለዋል። የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራው በዞኑ ባህል መሆኑን ተከትሎ በተለይም ከፍተኛ ተዳፋት በሆኑ የዞኑ መልክዓ ምድር የቡና ምርታማነትን በአማካይ በሄክታር ከ10 ኩንታል ማላቅ መቻሉን ተናግረዋል። በዚህም የውሃ መጠንን በማሳደግ በምርትና ምርታማነት የተገኘውን ውጤት ለማስቀጠል በተያዘው ዓመትም ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አንስተው አርሶ አደሩ ተሳትፎውን እንዲያጠናክር ጥሪ አቅርበዋል። በዞኑ በ132 ንዑስ ተፋሰሶች 67 ሺህ 402 ሄክታር መሬት በተቀናጀ የተፋሰስ ልማት እንደሚሸፈን ያነሱት ደግሞ የዞኑ ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ ተገኝ ታደሰ ናቸው። በዚህም ከ386 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ይሳተፋሉ ብለዋል። ለአንድ ወር በሚቆየው በዚሁ የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን ከቡና፣ ከእንሰትና ፍራፍሬ ልማት ጋር በማቀናጀት እንደሚተገበር ተናግረዋል። በዘመቻው ተሳታፊ የሆኑ አርሶ አደሮች ለኢዜአ እንዳሉት፤ የተፋሰስ ልማት ስራ የመሬት እርጥበትን በመጨመር የግብርና ምርታማነትን በማሳደጉ የእርሻ ሥራቸው አካል አድርገው እየተገበሩት ነው፡፡ አርሶ አደር ታምራት ታደሰ ፤ ባለፉት ዓመታት በተፋሰስ ልማት ያከናወኑት የእርከንና የአፈር ካባ ሥራ የመሬት መከላትን በማስቀረት እርጥበት መጨመሩን አንስተዋል። ይህም የእርሻ መሬታቸውን ለምነት በማሳደግ የቡናና እንሰት ምርታማነትን ማሳደጉን አንስተው በአሁኑ ወቅትም የእርሻ ሥራቸው አካል በማድረግ እየተገበሩት መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም ውሃን ማቆየት የሚችሉትን እርከንና የጉድጓድ ቁፋሮ በዘመቻ እየተገበሩ መሆኑን ገልጸዋል። የተፋሰስ ልማት የተራቆቱና ለአደጋ የተጋለጡ አካባቢዎች ወደ ቀድሞ ይዞታቸው እንዲመለሱ እገዛ ማድረጉን አርሶ አደሮቹ ተናግረዋል። ቀበሌያቸው ተዳፋት መሆኑን ተከትሎ ለም የእርሻ መሬታቸውን በጎርፍ ከመወሰድ በመከላከል ለግብርና ልማት አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። በተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ ማስጀመሪያ መርሃግብሩ ላይ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር)ን ጨምሮ የዞንና የሁሉም መዋቅሮች የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ አርሶ አደሮችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
የተፋሰስ ልማት ሥራ የመሬት ለምነትን በመጨመር ምርታማነትን አሳድጓል
Jan 23, 2026 236
ሃዋሳ፤ ጥር 15/2018 (ኢዜአ):-የተፋሰስ ልማት ሥራ የአፈር መሸርሸርን በማስቀረትና የመሬት ለምነትን በመጨመር ምርታማነታቸውን በማሳደጉ ልማቱን አጠናክረው መቀጠላቸውን የሲዳማ ክልል አርሶ አደሮች ገለጹ፡፡ አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ እንዳሉት ቀደም ሲል በተፋሰስ ልማት ያከናወኗቸው የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች የአፈር መሸርሸርን በማስቅረትና የመሬት ለምነትን በመጨመር ምርትና ምርታማነታቸውን እያሳደገው ነው። ተጠቃሚነታቸውን አጠናክሮ ለማስቀጠልም በአሁኑ ወቅትም የተፋሰስ ልማት ስራ እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ከአርሶ አደሮቹ መካከል አቶ ቶማስ መራሳ እንደገለጹት በየዓመቱ በተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ በመሳተፍ የአካባቢያቸውን ለምነት እየጠበቁ ነው፡፡ ተፋሰስ ልማቱ ምርታማነትን በማሳደግ ተጠቃሚ እያደረጋቸው በመምጣቱ በአሁኑ ወቅትም በቡድን ተደራጅተው ልማቱን እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ተከናውኖ ባገገሙ መሬቶችም ቡናና ፍራፍሬዎችን በማልማት ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ሌላው አርሶ አደር ጴጥሮስ ሶቾሳ በበኩላቸው በተፋሰስ ልማት ሥራው አርሶ አደሩ በንቃት እየተሳተፈና ተጠቃሚነቱን እያረጋገጠ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በአካባቢያቸው ከዚህ ቀደም ገላጣ የነበሩና የተጎዱ መሬቶች ማገገማቸውን ጠቅሰው፣ በእርሻ ማሳቸው የነበረውን ባህር ዛፍም በመንቀል የመሬታቸውን ለምነት እየጠበቁና ምርታማነት እያሳደጉ መምጣታቸውን ተናግረዋል። የተፋሰስ ልማት ሥራው ምርት የማይሰጡ መሬቶች ወደ ምርት እንዲገቡና የሥራ እድል እንዲፈጠር ማድረጉን የገለጹት ደግሞ ሌላው አርሶ አደር ሳሙኤል ጢሞቲዮስ ናቸው። ቀበሌያቸው ተዳፋታማ በመሆኑ ጎርፍ መሬታቸውን በመሸርሸር ለምነቱን እያጣ በመምጣቱ ከልማቱ ተጠቃሚ ሳይሆኑ መቆየታቸውን አስታውሰው፣ የተፋሰስ ልማት ሥራ ከተጀመረ ወዲህ በየዓመቱ ምርታማነታቸው እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። የሲዳማ ክልል እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ በበኩላቸው በክልሉ በየዓመቱ የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የተጎዳ መሬት እንዲያገግም ጉልህ አስተዋጾ እያደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል። የውሃ አማራጮችን በመጨመር የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ጉልህ ሚና በመጫወታቸው ልማቱ በየዓመቱ እየተጠናከረ መምጣቱንም ገልጸዋል። በዚህም በክልሉ በየጊዜው በሚካሄዱ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ የሚሳተፉ አርሶ አደሮች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በክልሉ በዘንድሮ የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራ ከ147 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚለማ ሲሆን በተለዩ 678 ንኡስ ተፋሰሶች ለ30 ተከታታይ ቀናት የሚቆይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እንደሚከናወን ታውቋል።
ኢትዮጵያ በውኃ ሀብት አስተዳደር እና በተፋሰስ ልማት ሥራዎች ውጤታማ ተግባራት እያከናወነች ነው
Jan 22, 2026 192
ነቀምቴ ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በውኃ ሀብት አስተዳደርና በተፋሰስ ልማት ሥራዎች ውጤታማ ተግባራት እያከናወነች መሆኑን የውኃና ኢነርጂ ሚኒስትር ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር) ገለጹ። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የ2018 በጀት ዓመት የ6 ወራት እቅድ አፈጻጸም ግምገማ በነቀምቴ ከተማ እየተካሄደ ነው። የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ኢተፋ (ዶ/ር)፣ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ባለፉት ዓመታት የውኃ ሀብትን በአግባቡ አልምቶ ጥቅም ላይ ለማዋል የተወሰዱ እርምጃዎች ውጤት እያስገኙ ነው። ኢትዮጵያ የምትከተለው ፍትሃዊና ምክንያታዊ የውኃ ሀብት አጠቃቀምና አስተዳደርም የልማት እንቅስቃሴን ለማፋጠን ጉልህ ሚና አለው ብለዋል። ኢትዮጵያ በውኃ ሀብት አስተዳደርና በተፋሰስ ልማት ስራዎች እየከናወነች ያለው ሥራ ተጨባጭ ውጤት ማምጣቱን በመግለጽ። በሌላ በኩል ሚኒስቴሩ በተፋሰስ ልማትና በቆላማ አካባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ስራዎች ተስፋ ሰጪ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን አንስተዋል። ከውሃ ሀብት በተጨማሪ የኢነርጂ ሀብትን በአግባቡ መለየትና ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባም አንስተዋል። በመድረኩ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የፌዴራልና የክልሎች እንዲሁም ሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች የውሃ እና ኢነርጂ ቢሮ ሀላፊዎች ተሳትፈዋል።
የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ጥቅምን በተግባር ስላየነው አጠናክረን እንቀጥላለን - አርሶአደሮች
Jan 22, 2026 325
አሶሳ፤ ጥር 14/2018 (ኢዜአ)፦ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ጥቅምን በተግባር በማየታቸው ተግባሩን አጠናክረው መቀጠላቸውን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የቡልድግሉ ወረዳ አርሶአደሮች ተናገሩ። በምዕራብ ወለጋ ዞን በ 487 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው የተፋሰስ ልማት የግብርና ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ መሰረት ሆኗል- ርዕሰ መስተዳድር ደስታ ሌዳሞ አርሶአደ ሂድር ኡስማን እንዳሉት፤ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ዘላቂ የመሬት አያያዝና አጠቃቀም እንዲኖር ከማድረግ በተጨማሪ የአካባቢውን የአየር ንብረት በማስተካከል ሚናው የጎላ ነው። ወይዘሮ ማርታ ዋቅቶላ በበኩላቸው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ መሠራት ከጀመረ ወዲህ በጎርፍ የሚወሰደው ለም አፈር በመቀነሱ ምርታማነታቸው እንዲጨምርና የአካባቢው ሥነ-ምኅዳርም መጠበቁን ተናግረዋል። የተፈጥሮ ፀጋን የማልማትና የመጠበቅ ስራው ተጠናክሮ ይቀጥላል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ከዚህ በፊት የተከናወነው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ የተራቆቱ አካባቢዎች መልሰው እንዲያገግሙ በማድረግ በደን እንዲሸፈኑ ማስቻሉን ያስረዱት ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጭ ቢራቱ ፉፋ ናቸው። ቀደም ሲል ከተሠራው የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ተጠቃሚነታቸውን ገልጸው፤ በቀጣይም አካባቢን ጠብቆ ለትውልድ የማስተላለፍ ተግባር ስለሆነ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አርሶ አደሮቹ ለኢዜአ ገልጸዋል። የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትልና የተፈጥሮ ሀብት ልማት ዘርፍ ኃላፊ አብዱልከሪም ሙሳ፤ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ የአካባቢውን ሥነ-ምኅዳር ይጠብቃል፤ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብም በደለል እንዳይሞላ ይረዳል ብለዋል። ስለዚህ አርሶአደሩ ተሳትፎውን አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ አሳስበዋል። ዘንድሮው በክልሉ ከ57 ሺህ ሔክታር በላይ ማሳ የአፈርና ውኃ ጥበቃ ሥራ ለማከናወን መታቀዱን አውስተዋል።
በምዕራብ ወለጋ ዞን በ 487 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ ነው
Jan 22, 2026 279
ጊምቢ፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ወለጋ ዞን በ487 ተፋሰሶች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑ የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ በምዕራብ ወለጋ ዞን ግብርና በጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ቡድን መሪ አቶ ፍቅሩ ብርሃኑ እንዳሉት፣ በዞኑ በ487 ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች እየተከናወኑ ነው፡፡ ባለፉት አመታት በዞኑ በተከናወኑ የተለያዩ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች በመጡ ተጨባጭ ለውጦች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ በማድረጋቸው ለዘንድሮ ተፋሰስ ልማት ስራዎች በነቂስ ወጥተው እየተሳተፉ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል፡፡ በዞኑ ከ273 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት የሚሸፍን የአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራ መካሄድ ጀምሯል በተለይም እየተከናወኑ ባሉ የተፋሰስ ልማት ስራዎች የእርከን ስራና ቀደም ብለው የለሙ ተፋሰሶች ከእንስሳትና ከሰው ንክኪ ነጻ እንዲሆኑ ጥበቃ ይደረግለታል ብለዋል። በዞኑ በላሎሳቢ፣ በመነስቡ፣ በጊምቢና ሆማ ወረዳዎች በእስካሁኑ እንቅስቃሴ በእርከን ስራ የተሻለ ስራ መሰራቱን ገልጸዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት በተፋሰስ ልማት መርሃ ግብር በተከናወኑት ስራዎች የተራቆቱ አካባቢዎች ወደ ልምላሜ መመለሳቸውን እና በዘንድሮው የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ላይ በንቃት እንዲሳተፉ ምክንያት እንደሆናቸው የሚናገሩት ደግሞ አርሶ አደር አምቢሳ ጉዲና ናቸው፡፡ ልማቱ ቀደም ሲል በአፈር መሸርሸር ምክንያት ምርታማነት ቀንሶ የነበረው የእርሻ መሬታቸው አሁን ላይ ማገገሙን ጠቅሰዋል። አርሶ አደር ከኔሳ አሙማ በበኩላቸው፤ ባለፉት አመታት በተከናወኑት የእርከንና ሌሎች የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራዎች በአካባቢያቸው ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም በዘንድሮ የበጋ ወራት የእርከን ልማት ስራዎች ላይ ከሌሎች አርሶ አደሮች ጋር በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል፡፡