አካባቢ ጥበቃ - ኢዜአ አማርኛ
አካባቢ ጥበቃ
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል ላይ ማዕከል ያደረገ ውጤታማ የልማት አቅጣጫ ላይ ናት
Apr 27, 2026 231
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል ላይ ማዕከል ያደረገ ውጤታማ የልማት አቅጣጫ ላይ ናት ሲሉ የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ ገለጹ። የአየር ንብረት ኢንቨስትመንት ፈንድስ(CIf) ከኢትዮጵያ መንግሥት እና የአፍሪካ ልማት ባንክ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ዓለም አቀፍ የልምድ ልውውጥ ጉባኤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። በጉባኤው ላይ ምሁራን፣የልማት አጋሮችና ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ጨምሮ አምባሳደሮችና የሀገራት ተወካዮች ተገኝተዋል። ለሶስት ቀናት በሚቆየው በዚህ ጉባኤ ላይ የተለያዩ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ረገድ ያገኟቸው ውጤቶች ላይ ተሞክሮዎችን አቅርበው የልምድ ልውውጥ እንደሚያደርጉ ይጠበቃል። የገንዘብ ሚኒስትር አቶ አህመድ ሽዴ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ የዕድገት ራዕይና አቅጣጫ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል ላይ ማዕከል ያደረገ ነው። ለዚህም ታዳሽ ሃይልን ማስፋፋት፣የውሃ አቅርቦት ማሻሻል፣ የተራቆቱ መሬቶች መልሰው እንዲያገግሙ በማድረግ የማህበረሰቡን የመቋቋም አቅም የሚያሳድጉ ውጤታማ ተግባራት መከናወኑን አብራርተዋል። የአዲስ አበባ የኮርደር ልማትና የወንዝ ዳር ልማት ስራዎች ከተማዋን ዘመናዊ ከማድረጋቸውም ባሻገር እድገት ከአካባቢ ጥበቃ ጋር በተናበበ መልኩ እንዴት እንደሚከወን ማሳያ ነው ብለዋል። መንግሥትም ከአየር ንብረት ለውጥ ኢንቨስትመንት ፈንድስ ጋር በጋራ በመሆን በኢትዮጵያ በአማራጭ ሃይል አቅርቦቶች እና ተፈጥሮን መሰረት ያደረጉ መፍትሔዎች ላይ ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑንም አመልክተዋል። የዛሬው የልምድ ልውውጥ ጉባኤ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ዙሪያ ያላትን ተሞክሮ ለማካፈል፤ ከሌሎች ተሳታፊዎችም ለመማር ዝግጁ ናት ሲሉም ገልጸዋል። የአየር ንብረት ኢንቨስትመንት ፈንድስ(CIF) ዋና ስራ አስፈጻሚ ታሪዬ ባድጌሲን በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በቢሊዮን የሚቆጠሩ ችግኞችን በመትከል በአረንጓዴ አሻራ አርዓያ የሚሆን ተግባር መፈጸሟን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ሁለተኛውን የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ከዚህ ቀደም ስኬታማ በሆነ መንገድ ማስተናገዷም በዘርፉ ያላትን የላቀ ተሞክሮ ያሳያል ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ፈንድስ ከኢትዮጵያ መንግሥት ጋር በጋራ የሚያከናውናቸውን ተግባራት አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።
በአማራ ክልል ከ22 ሚሊዮን በላይ የቡናና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች ለተከላ ተዘጋጅተዋል
Apr 27, 2026 165
ባህርዳር፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በመጪው ክረምት ለሚካሄደው የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከ22 ሚሊዮን በላይ የቡናና የሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸው ተገለጸ። በቢሮው የሆርቲካልቸር ባለሙያ አቶ አወቀ ዘላለም ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክልሉ ተስማሚ ስነ-ምህዳርና የአየር ንብረት ያላቸውን አካባቢዎች በመለየት ቡናና ሌሎች ፍራፍሬዎችን በክላስተር የማልማት ስራ እየተካሄደ ነው። በተያዘው በጋ ወቅትም ከፍተኛ ምርት የሚሰጡና በሽታን የሚቋቋሙ ከ22 ነጥብ አራት ሚሊዮን በላይ የቡናና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ለተከላ ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል ወደ 12 ነጥብ 2 ሚሊዮን የሚጠጋው የቡና ችግኝ ሲሆን ቀሪው ደግሞ የቆላና የደጋ ፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ተናግረዋል። ክልሉን በቡናና ፍራፍሬ ልማት ሞዴል ለማድረግም ሽፋኑንና ምርታማነቱን በማሳደግ ላይ በማተኮር የአርሶ አደሩ ዘላቂ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። ለመጪው ክረምት ለተከላ እየተዘጋጀ ያለው ችግኝም ከ32 ሺህ ሄክታር በላይ በሚሆን መሬት ላይ የሚተከል መሆኑን አስረድተዋል። በምዕራብ ጎጃም ዞን የጃቢ ጠህናን ወረዳ አርሶ አደር ተፈራ መለሰ ፤ ባለፉት ዓመታት በአንድ ሄክታር መሬት ላይ ቡናን የማልማት ስራ መስራታቸውን ጠቅሰዋል። በመጪው የክረምት ወቅትም በተጨማሪ ሩብ ሄክታር መሬት ላይ የቡና ችግኝን በኩታ ገጠም ለመትከል አቅደው እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል። የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በመትከል የተሻለ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን የገለፁት ደግሞ የዚሁ ወረዳ አርሶ አደር ውበት ተስፌ ናቸው። ባለፈው ዓመት የክረምት ወቅት ከተተከሉ ወደ 17 ነጥብ 7 ሚሊዮን የሚጠጋ ቁጥር ያላቸው የቡና፣ የቆላና ደጋ ፍራፍሬ ችግኞች 93 ነጥብ 5 በመቶው መጽደቁን የቢሮው መረጃ ያመለክታል፡፡
ለአረንጓዴ አሻራ ልማት ስኬት የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ሚና ላቀ ነው
Apr 24, 2026 125
ሆሳዕና ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፦ከአካባቢ ጥበቃ ባለፈ ለምግብ ዋስትና መሰረት ለሆነው የአረንጓዴ አሻራ ልማት ስኬት የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች የላቀ ሚናቸውን ማስቀጠል እንዳለባቸው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ቢሮ ገለጸ፡፡ የክልሉ ደንና አካባቢ ጥበቃ ልማት ቢሮ ከክልሉ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ጋር በመተባበር በአረንጓዴ አሻራ ልማት ዙሪያ ለሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች በሆሳዕና ከተማ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ሰጥቷል፡፡ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ ኡስማን ሱሩር እንደገለጹት፤ በክልሉ የአረንጓዴ አሻራ ትግበራ ከደን ልማቱ ባለፈ የስነ ምግብ ዋስትና መሰረት እየሆነ መጥቷል። በልማቱ ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ያላቸውንና ለምግብ የሚሆኑ የፍራፍሬ ተክሎችን በብዛትና በስፋት የማልማት ሥራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ለተፈጥሮ ሃብት ጥበቃና ለምግብ ዋስትና መሰረት ለሆነው የአረንጓዴ አሻራ ልማት ስኬት የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች ሚናቸውን አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ አንስተዋል። የስልጠናው ዓላማም የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች በእውቀትና መረጃ ላይ የተመሰረተ መረጃ ለህዝብ ተደራሽ ማድረግ እንዲችሉ መሆኑን ገልጸዋል። የክልሉ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ ዘሪሁን እሸቱ፤ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ባለሙያዎች በዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ሥራዎችን በሚገባ ተገንዝበው የተሟላ መረጃ ለህዝብ ተደራሽ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። ለዚህም መሰል የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች ወሳኝ እንደሆኑ አንስተው በቀጣይም በሙያቸው የሚያደርጉትን አስተዋጽኦ በማስቀጠል ልማቱን እንዲያጠናክሩ አስገንዝበዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የተለያዩ የሚዲያ ተቋማት፤ የኮሙኒኬሽን አመራሮችና ባለሙያዎች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተሻለ የእርጥበት ሁኔታ ይኖራቸዋል
Apr 24, 2026 127
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 16/2018(ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተሻለ የእርጥበት ሁኔታ እንደሚኖር የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ፡፡ የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በሚቀጥሉት አስር ቀናት የሚኖረውን የአየር ሁኔታ ትንበያ አስመልክቶ ለኢዜአ መግለጫ ልኳል፡፡ በዚህም በሚቀጥሉት አስር ቀናት በርካታ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተሻለ የእርጥበት ሁኔታ እንደሚያገኙ አመላክቷል፡፡ በመግለጫው በደቡብ የሀገሪቱ ክፍል፣ የስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎች፣ መካከለኛው፣ ሰሜን ምስራቅ እና ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ እንዲሁም ሰሜን ምዕራብ እና ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተሻለ የእርጥበት ሁኔታ እንደሚኖራቸው አስታውቋል፡፡ በእነዚህ አካባቢዎች የሚኖረው ከመካከለኛ እስከ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ ለቋሚ ተክሎች ዕድገት፣ ለግጦሽ ሳርና ለውሃ አቅርቦት መሻሻል ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ገልጿል። በሌላ በኩል ከዝናቡ ጋር ተያይዞ የመሬት መንሸራተት፣ የአፈር መሸርሸር እና ድንገተኛ ጎርፍ አደጋዎች ሊከሰት ስለሚችል ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል ብሏል፡፡ በተጨማሪም በተደፋታማ ማሳዎች ላይ ውሃ መተኛት፣ የሰብል በሽታና ተባይ መከሰት እንዲሁም የአረም መስፋፋት ሊከሰት እንደሚችል ጠቅሷል፡፡ በዚህም በከተሞች በቆሻሻ የተደፈኑ የውሃ ማፋሰሻ ቱቦዎችን ማጽዳትና የቅድመ ጥንቃቄ ስራዎችን መሥራት ይገባል ብሏል በመግለጫው፡፡ የአፈርና ውሃ እቀባ ስራዎች እንዲሁም የእርከን ስራዎችን ማጠናከር፣ የሰብል በሽታና አረምን አስቀድሞ መከላከል እንዲሁም የእንስሳት መኖ መሰብሰብ እንደሚገባም አመላክቷል፡፡ በተጨማሪም ዝቅተኛ እርጥበት በሚገኝባቸው አካባቢዎች የዝናብ ውሃን በማሰባሰብና ደጋፊ መስኖን በመጠቀም የትነት መጠን የሚያስከትለውን ጉድለት መሙላት እንደሚገባ አስታውቋል፡፡ በአባይ፣ ባሮ አኮቦ፣ የላይኛው ኦሞ ጊቤ፣ ገናሌ ዳዋ እና ስምጥ ሸለቆ ተፋሰሶች ላይ ከአነስተኛ እስከ ከፍተኛ የገፀ-ምድር ውሃ ፍሰት እንደሚኖርም በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ይህም ለኃይል ማመንጫ፣ ለመስኖና ለመጠጥ ውሃ አቅርቦት መሻሻል ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥር ጠቁሞ፤ ህብረተሰቡ የጎርፍ አደጋን ለመከላከልና የሚገኘውን እርጥበት በአግባቡ መጠቀም እንደሚገባውም አሳስቧል፡፡
በብሔረሰብ አሥተዳደሩ ሥነ-ምኅዳርን መሠረት ያደረጉ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት እየተደረገ ነው
Apr 24, 2026 116
ሰቆጣ፤ ሚያዝያ 16/2018 (ኢዜአ)፡- በመጪው ክረምት ሥነ-ምኅዳርን መሠረት ያደረጉ ችግኞችን ለመትከል የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የዋግኽምራ ብሔረሰብ አሥተዳደር ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የደን ባለሙያ ታደሠ መሳይ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ አሥተዳደሩ ዝናብ አጠር ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የተፈጥሮ ሃብት ሥራና የደን ልማት ተግባራት በከፍተኛ ትጋት እየተሠራበት ነው። በዚህም እስካሁን 3 ነጥብ 7 ሚሊየን ችግኞችን ለተከላ ዝግጁ ማድረግ መቻሉን ጠቁመው፤ ችግኞቹ ምኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውና ሀገር በቀል ናቸው ብለዋል። በበጋው ወራት የአፈርና ውኃ ዕቀባ ሥራ የተሠራበትን ጨምሮ ከ2 ሺህ 130 ሔክታር በላይ መሬት በመለየት የችግኝ መትከያ ጉድጓድ የማስቆፈር ሥራ እየተሠራ መሆኑንም አስረድተዋል። ባለፉት ዓመታት ሥነ-ምኅዳሩንና የአየር ንብረቱን መሠረት ያደረጉ ችግኞችን በመትከል አካባቢውን ወደ ምርታማነት የመለወጥ ሥራ ውጤት በማሳየቱ፤ ሕብረተሰቡ ለተፈጥሮ ሃብት ሥራ ከፍተኛ ፍላጎት ማሳየቱን ጠቁመዋል።
በምሥራቅ ወለጋ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በስፋት እየተዘጋጁ ነው
Apr 23, 2026 124
ነቀምቴ፤ ሚያዝያ 15/2018(ኢዜአ)፦በምሥራቅ ወለጋ ዞን በመጪው ክረምት የሚተከሉ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በስፋት እየተዘጋጁ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት አስታወቀ። በጽሕፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ደሳለኝ በለጠ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሐ ግብር ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች በስፋት እየተዘጋጁ ነው። በዘንድሮው መርሐ ግብር ለሁሉም የችግኝ ዓይነቶች ትኩረት ቢሰጥም፣ ይበልጥ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ዝርያዎች ላይ ትኩረት ተደርጓል ነው ያሉት። እየፈሉ ከሚገኙት ችግኞች መካከል አትክልትና ፍራፍሬ፣ የደንና ጥምር ደን ዝርያዎች፣ ቀርከሃ፣ የእንስሳት መኖ የሚገኙበት መሆኑን ነው የተናገሩት። የእጽዋት ስብጥሩ ከአካባቢው አየር ንብረት ጋር የሚስማማና በአጭር ጊዜ ውስጥ ውጤት የሚሰጡ መሆናቸውን ገልጸዋል። ካለፉት ዓመታት ተሞክሮ በመነሳት የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የጉድጓድ ዝግጅት መጀመሩን የጠቆሙት አቶ ደሳለኝ፤ የአየር ንብረት ጥናት፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ እንዲሁም የሕብረተሰቡን ተሳትፎ የሚያሳድጉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። ለዘንድሮው ተከላ የሚውል 107 ሺህ ሄክታር መሬት የተዘጋጀ ሲሆን፣ በዞኑ በሚገኙ 2 ሺህ 194 የመንግሥትና የግል የችግኝ ጣቢያዎችም የችግኝ እንክብካቤ ሥራው ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች በበኩላቸው ችግኝ መትከል ከመደበኛ መርሐ ግብር ባለፈ የሥራ ባሕላቸው እየሆነ መምጣቱን ይናገራሉ። አስተያየታቸውን ከሰጡት መካከል ወይዘሮ አዲስዓለም በለጠ ባለፉት ዓመታት በተተከሉ ችግኞች በአካባቢው የተፈጥሮ ሀብት ለውጥ መታየቱን ገልጸዋል። አቶ ተሰማ መኮንንም በተመሳሳይ ቀደም ሲል ለደን የነበረው ዝቅተኛ አመለካከት ተቀይሮ፣ ዛሬ ሕብረተሰቡ የተራቆቱ ቦታዎችን መልሶ በማልማትና በመንከባከብ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ለዘንድሮው ተከላም አስፈላጊውን ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን ጠቁመዋል።
የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት በሚደረገው ጥረት በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው
Apr 22, 2026 139
ሐዋሳ፤ ሚያዝያ 14/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት በአፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት በሚደረገው ጥረት በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን የአፍሪካ አረንጓዴ አብዮት ጥምረት (AGRA) የቦርድ ሊቀመንበር ኃይለማርያም ደሳለኝ ገለጹ። ሊቀመንበሩ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂ ከሀገር ባለፈ አህጉራዊ የልማት ትብብርና ትስስርን መሰረት ባደረገ መልኩ በስኬት መቀጠሉን አንስተዋል። ኢትዮጵያ የአረንጓዴ ልማት ስትራቴጂዋ ከተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ እና የአየር ንብረት ለውጥን ከመከላከል ባለፈ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑንም ገልጸዋል። በተለይም ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የልማት ሥራዎች አስደናቂ መሆናቸውን አውስተው፤ እንደ ሀገር ትልቅ ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን ተናግረዋል። ባለፉት ዓመታት በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ችግኞች መተከላቸው የተፈጥሮ ሃብትን ከመጠበቅና የአየር ንብረት ለውጥን ከመከላከል ባለፈ የምግብ ዋስትና መሰረት መሆናቸው በተግባር ታይቷል ብለዋል። በመሆኑም የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት በአፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት በሚደረገው ጥረት በምሳሌነት የሚጠቀስ መሆኑን ነው ያመላከቱት። ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ላይ ትኩረት ተደርጎ መሠራቱም ለግብርና ልማትና ምርታማነት መሰረት እየሆነ መጥቷል ነው ያሉት። የዘርፉ ልማት ቀጣይነትን የሚጠይቅ በመሆኑ ችግኞችን መትከል እንዳለ ሆኖ፤ የተተከሉትን የመጠበቅና የመንከባከብ ልምድ እየዳበረ መሄድ እንዳለበትም ጠቁመዋል።
በከተማ አስተዳደሩ የተከናወኑ የአረንጓዴ አሻራ ሥራዎች አርሶ አደሩን ተጠቃሚ አድርገዋል
Apr 21, 2026 324
ወላይታ ሶዶ፤ሚያዚያ 13/2018(ኢዜአ)፦በወላይታ ሶዶ ከተማ በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የአርሶ አደሩን ተጠቃሚነት እያረጋገጡ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ። በከተማ አስተዳደሩ "አረንጓዴ አሻራ ለተምሳሌት ሀገር ኢትዮጵያ" በሚል መሪ ቃል የዘንድሮ የበልግ ወቅት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር በመርካቶ ክፍለ ከተማ ቦሳ ዝጋ ቀበሌ ተካሂዷል። የከተማው ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማርያም በመርሃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት ባላፉት የለውጡ ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተከናወኑ የልማት ሥራዎች የአርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት አረጋግጠዋል። በመርሀ ግብሩ የተተከሉ ችግኞች የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ በተጨማሪ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከልና ሚዛኑን ለመጠበቅ እያገዙ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም የችግኝ ተከላ ሥራውን ለማስቀጠል የቡና፣ የእንሰት የአቮካዶና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል ሙሉ ዝግጅት በማድረግ ወደ ሥራ መገባቱንም ተናግረዋል። የወላይታ ሶዶ ከተማ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ንጋቱ ቡሹራ በበኩላቸው ባለፉት ዓመታት በተሰሩ የአረንጓዴ አሻራ ስራዎች የአርሶ አደሩን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ተችሏል። ለዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ለተከላ ከተዘጋጁ ችግኞች ውስጥ 150 ሺህ የሚሆኑት የተሻሻሉ የቡና ዝርያ ችግኞች መሆናቸውንም አመልክተዋል። ከዚህ በተጨማሪ ምርታማነታቸው በምርምር የተረጋገጡ የእንሰት፣ የአቮካዶ እና ሌሎች የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ነው የገለጹት። የሚተከሉ ችግኞች ውጤታማ እንዲሆኑም የተጠናከረ የባለሙያዎች ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል። በመርሀ ግብሩ ላይ ከተሳተፉ አርሶ አደሮች አቶ ደበላ ዳና እና አቶ ኤልያስ ጁና በውሃ ገብ መሬቶችና እና በእርሻ ማሳቸው ላይ ባህር ዛፎችን እና ያረጁ ቡናዎችን በመተካት ልማቱን ማከናወናቸውን ጠቁመዋል። በችግኝ ተከላው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው ፍራፍሬዎችን በመትከል ተጠቃሚ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ረዳት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ተሰማ በበኩላቸው በዞኑ ባለፉት ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች መተከላቸውን አንስተዋል። በዘንድሮ የአረንጎዴ አሻራ መርሃግብርም የቡና ችግኝ በስፋት ለመትከል ዝግጅት መደረጉን ነው የገለጹት። አርሶ አደሮችም በመርሀግብሩ ቡናና ሌሎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው የፍራፍሬ ችግኞችን ተክለው በመንከባከብ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸውን እንዲያሳድጉ አሳስበዋል። በችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ላይ የዞንና የከተማ የመንግስት ሥራ ኃላፊዎች፣ ባለሙያዎች እንዲሁም አርሶ አደሮች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የወሰደቻቸው ተጨባጭ እርምጃዎች ውጤት እያስገኙ ነው
Apr 21, 2026 181
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም የወሰደቻቸው ተጨባጭ እርምጃዎች ውጤት እያስገኙ መሆኑን የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ ከአፍሪካ የሚቲዎሮሎጂ ሶሳይቲ ጋር በመተባበር ለመጀመሪያ ጊዜ ያዘጋጀውን ሳይንሳዊ ኮንፈረንስ በአዲስ አበባ እያካሄደ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተርና በዓለም ሚቲዎሮሎጂ ድርጅት የአፍሪካ አህጉር ፕሬዚዳንት አቶ ፈጠነ ተሾመ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም ለዘርፉ ተስማሚ የሆኑ የኃይል አማራጮችንና የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን በተግባር እያከናወነች ትገኛለች፡፡ ለዚህም እንደ አብነት ከሚጠቀሱት መካከልም ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የታዳሽ ኃይል ልማት ተምሳሌትና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ግንባታ ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር፣ በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተተገበረ ያለው የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና የደን ልማት ስራዎች ተጨባጭ መፍትሄዎች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ድንበር ተሻጋሪ በመሆኑ ተጽዕኖውን ለመቋቋም የጋራ ጥረትና ትብብር መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ከኮንፈረንሱ ለአፍሪካ ውጤታማ የሆኑ ሳይንሳዊ መፍትሄዎች እንደሚገኙም ገልጸዋል፡፡ የአፍሪካ የሚቲዎሮሎጂ ሶሳይቲ የቦርድ ሰብሳቢ ቡሩሃኒ ናይንዚ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ ሶሳይቲው የተቋቋመው ሀገር አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ ማህበራትን ለማጠናከርና በዘርፉ ያሉ ባለሙያዎችን ለማስተሳሰር መሆኑን ገልጸዋል። ሳይንሳዊ ኮንፈረንሱ በአካባቢ ጥበቃ፣ በአየር ትንበያና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ የሚሰሩ ተቋማትና ባለድርሻ አካላትን እንደሚያገናኝም ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም የልምድና የዕውቀት ልውውጥ በማድረግ የባለሙያዎችን አቅም እንደሚገነባ ጠቅሰው በአፍሪካ የሚቲዎሮሎጂ ሳይንስ እድገት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውም ጠቁመዋል፡፡ ይህ ኮንፈረንስ ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ዙሪያ ያላትን ተሞክሮ ለማካፈል እንደሚረዳም ተጠቁሟል፡፡
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑት የሀገሪቱ አካባቢዎች የዝናብ ቀጣይነት ይኖራል
Apr 20, 2026 123
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2018(ኢዜአ)፦ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑት የሀገሪቱ አካባቢዎች ላይ የዝናብ ቀጣይነት እንደሚኖረው የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው ከሚቲዎሮሎጂ ክስተቶች ጋር ተያይዞ ወቅታዊ ዝናብ ቀስ በቀስ ወደ ምዕራብ አጋማሽ የሀገሪቱ ክፍሎች እየተስፋፋ እንደሚሄድ ገልጿል። በዚህም በደቡብ፣ ደቡብ ምዕራብ፣ ምዕራብ፣ ምስራቅ እንዲሁም በስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች የተሻለ ገጽታ ይኖራቸዋል ብሏል። በመሆኑም በበልግ አብቃይ አካባቢዎች በርካታ ቦታዎችን የሚሸፍን ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ገልጿል። በተጨማሪም በውሃ አካላትና በአካባቢ አየር ውስጥ ከሚጠናከሩት የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች በመነሳት በደቡብ እና ደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ አካባቢዎች ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ አሃዛዊ የትንበያ መረጃዎች ይጠቁማሉ ብሏል። አርሶ እና አርብቶ አደሮች እንዲሁም የሚመለከታቸው አካላት የሚጠበቁ መልካም ሁኔታዎችን በአግባቡ እንዲጠቀሙና የግብርና ተኮር ሚቲዎሮሎጂ ምክረ ሀሳቦችን መተግበር እንደሚገባ አስታውቋል። ይህም ለበልግ ሰብሎች እና ቋሚ ተክሎች እድገት አዎንታዊ ሚና ያለው ሲሆን ለአፈር እርጥበት በመጨመር ለእርሻ እንቅስቃሴ ምቹ ሁኔታ ይፈጥራል ነው ያለው። በሚቀጥሉት አስር ቀናት በአብዛኞቹ የሀገሪቱ ተፋሰሶች ላይ የሚጠበቀው ዝናብ የገጸ ምድር ውሃ ፍሰትን እንደሚያሻሽልም ጠቁሟል።
በምስራቅ ጎጃም ዞን በአረንጓዴ አሻራው ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው አገር በቀል ችግኞች ተዘጋጅተዋል
Apr 20, 2026 136
ደብረ ማርቆስ፤ሚያዚያ 12/2018 (ኢዜአ)፦በምስራቅ ጎጃም ዞን በአረንጓዴ አሻራ የሚተከሉ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው አገር በቀል ችግኞች በስፋት መዘጋጀታቸውን የምስራቅ ጎጃም ዞን የተፈጥሮ ሃብት መምሪያ አስታወቀ። በአረንጓዴ አሻራው የሚተከሉት ችግኞችም የተለያዩ ዝርያ ያላቸው መሆኑን በመምሪያው የተፈጥሮ ሃብት ቡድን መሪ አቶ ንጉሴ ሽመልስ ለኢዜአ ገልጸዋል። በዘንድሮው ዓመት በአረንጓዴ አሻራና በመደበኛው የክረምት የችግኝ ተከላ መርሃ ግብር ከ52 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን የተራቆተ መሬት ላይ ችግኞች እንደሚተከሉም ነው ያስረዱት። ከተዘጋጁት ችግኞች ውስጥም የኮሶ፣ የግራር፣ የወይራ፣ የጌሾ፣ የዋንዛ፣ የባህር ዛፍ፣ የሳስቫኒያ፣ የዲክረንስ፣ የፈረንጅ ጽድና ሌሎች የችግኝ ዓይነቶች እንደሚገኙበት ጠቁመዋል። ችግኞቹን ማዘጋጀት የተቻለውም ከ38 ሺህ በላይ በሚሆኑ የመንግስት፣ የማህበራትና የግል ችግኝ ጣቢያዎች መሆኑንም ነው ያስታወቁት። እንደ መምሪያው ገለጻ፥ በበጀት ዓመቱ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የሚተከሉ ከ261 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ ተከናውኗል።
በምስራቅ ቦረና እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም የችግኝ ተከላ እየተከናወነ ነው
Apr 20, 2026 136
ነገሌ ቦረና፤ ሚያዝያ 12/2018 (ኢዜአ፡- በምስራቅ ቦረና ዞን እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ተከላ እየተከናወነ መሆኑ ተገለፀ። በዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ አልዬ አረባ ፤በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች ከ32 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን ለማፍላት ታቅዶ ሲሰራ ቆይቷል። እስካሁን በተካሄደው እንቅስቃሴ ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን በመቋቋም ኢኮኖሚያዊ ጥቅም የሚያስገኙ ከ25 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ለማዘጋጀት መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ከተዘጋጁት ችግኞች መካከል የደን ዛፍ፣ የተለያዩ ፍራፍሬዎች እና የእንስሳት መኖ የሚሆኑት ዋነኞቹ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የተዘጋጁት ችግኞች በዞኑ ቆላማ ወረዳዎች ከመጋቢት አጋማሽ እስከ ሚያዝያ መጨረሻ ድረስ የሚጥለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም የሚተከሉ መሆኑን ተናግረዋል። እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀምም እስካሁን በ 2 ሺህ 83 ሄክታር መሬት ላይ ችግኞች መተከላቸውንም ነው ያስታወቁት። በችግኝ ተከላው በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ አደጋ የተራቆተ ከ7 ሺህ 600 ሄክታር በላይ መሬት በመከለል ለማልማት ትኩረት መሰጠቱን አመላክተዋል። በዘላቂ ልማት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እየተካሄደ ባለው የአረንጓዴ አሻራ እንቅስቃሴ ከ159 ሺህ በላይ ህዝብ እየተሳተፈ መሆኑንም ጠቁመዋል። በዞኑ እየተስፋፋ የመጣው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በየዓመቱ የሚከሰተውን ድርቅና የአካባቢ መራቆት ለመከላከልና ለመቋቋም ማስቻሉን አክለዋል። መርሃ ግብሩ ለዞኑ ህዝብ መሰረታዊ ችግር የነበረውን የመጠጥ ውሀና የእንስሳት መኖ እጥረት እያቃለለ መምጣቱንም ጠቅሰዋል። በዚህም በየዓመቱ ለዞኑ ህዝብ ከመንግሥት ሲቀርብ የነበረው የመጠጥ ውሀና የእንስሳት መኖ ድጋፍ ሙሉ ለሙሉ ለማስቀረት ማስቻሉን አብራርተዋል። በዝናብ አጠርና ቆላማ ወረዳዎች የተጀመሩት የበጋ መስኖ፣ የተፋስስ ልማትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ተግባራት የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ ረገድ ሁለንተናዊ እገዛ ማድረጋቸውን አብራርተዋል።
ኮፕ 32 ዘላቂ ትሩፋት ያለው ሆኖ እንዲያልፍ ለማድረግ ይሰራል - ዓለምጸሐይ ጳውሎስ
Apr 18, 2026 214
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2018 (ኢዜአ)፦ 32ኛው የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ32) ሂደት ዘላቂ የሆነ ትሩፋት ያለው ሆኖ እንዲያልፍ ለማድረግ እንደሚሰራ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሐይ ጳውሎስ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በ32ኛው የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ32) ብሔራዊ ኮሚቴ የተከናወኑ ሥራዎችን ገምግመዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የካቢኔ ጉዳዮች ሚኒስትር ዓለምጸሐይ ጳውሎስ በዚሁ ወቅት የኮፕ32 መሠረተ ልማት፣ ሎጂስቲክስ እና ኦፕሬሽን ግብረ ኃይል የተከናወኑ ተግባራትን እና ትኩረት የሚፈልጉ ጉዳዮችን በሚመለከት ለኮፕ32 ብሔራዊ ኮሚቴ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በማብራሪያቸውም የግብረ ኃይሉ ዓላማ ጉባዔው ከመካሄዱ በፊት አስፈላጊ የሆኑ ጉዳዮችን በማሟላት፤ ጉባዔው በሚካሄድበት ወቅት የተሳለጠ እንዲሆን እንዲሁም ከተጠናቀቀ በኋላ ትውልድ ተሻጋሪ የሆነ ዕሴት አሳርፎ ማለፍ እንዲችል ማድረግ ነው ብለዋል። በዚህም ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ እና መስፈርቶችን የሚያሟሉ መሠረተ ልማቶች የሚገነቡ እንዲሁም ከተለያዩ አካላት የሚሰባሰቡ አስፈላጊ ጉዳዮች መኖራቸውን ጠቁመዋል። ደኅንነቱ የተጠበቀ፣ የተሳለጠ እና ስኬታማ ጉባዔ ከማካሄድ በተጨማሪ ወደ ትውልድ መሻገር የሚችሉ፣ ዘላቂ እና ለቀጣይ ስራዎች አጋዥ የሚሆኑ መሠረተ ልማቶች መገንባትን ታሳቢ ያደረገ ዓላማን በመያዝ እየተሰራ ነው ብለዋል። ግብረ ኃይሉ መሠረታዊ የሚባሉ ግቦችን በመለየት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልጸው፤ የሚገነቡ መሠረተ ልማቶች ዓለም አቀፍ መስፈርቶችን የሚያሟሉ እና ጉባዔውን የሚያሳልጡ መሆናቸውን ማረጋገጥ የመጀመሪያው ግብ መሆኑን አመላክተዋል። የተገነቡ መሠረተ ልማቶች እንግዶች በጉባዔው ለመሳተፍ ሲመጡ ከአቀባበል ጀምሮ እስከሚሸኙበት ጊዜ ድረስ ደረጃውን የሚመጥን እንቅስቃሴዎች እንዲኖሩ በማድረግ ስኬታማ ጉባዔ እንዲካሄድ መሠረታዊ ጉዳዮችን የያዘ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህ ሂደት ነባሩ የከተማ እንቅስቃሴ እና የሕብረተሰብ አገልግሎት እንደተጠበቀ ሆኖ ነባሩን ሳይረብሽ አዲስ የሚመጣውን መቋቋም የሚችል የማይበገሩ መሠረተ ልማቶች መኖራቸውን የማረጋገጥ ግብ ሌላኛው ትኩረት የተደረገበት እንደሆነ መግለጻቸውን ኤፍ ኤም ሲ ዘግቧል። በሂደቱ የሚፈጠሩ አቅሞች በተለይም ወጣቶች በሂደት ውስጥ እንዲያልፉ በማድረግ የሀገር ውስጥ አቅምን መገንባት የሚያስችል ስራ እንደሚሰራም አብራርተዋል። በተጨማሪም ሙሉ ሂደቱ ዘላቂ የሆነ ትሩፋት ያለው ሆኖ እንዲያልፍ ማድረግን ታሳቢ በማድረግ እንደሚሰራ ገልጸው፤ ጉባዔው ከተለያዩ ጉዳዮች አኳያ ደኅንነቱ የተጠበቀ ሆኖ እንዲካሄድ የሚያስችል ግቦችን በመያዝ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በዞኑ የበጋ ወራት የተቀናጀ ተፋሰስ ልማት ሥራዎች ምርታማነት እንዲጨምር አድርገዋል
Apr 18, 2026 127
አዳማ፤ ሚያዚያ 10/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የበጋ ወራት የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጋቸውን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የጽህፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንዳስታወቁት በዞኑ በየዓመቱ የተከናወኑ የተፋሰስ ልማት ሥራዎች የአካባቢ መራቆትን ከማሻሻል ባለፈ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል። ህብረተሰቡን በማሳተፍ የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎቹ የውሃ ምንጮች እንዲጎለብቱ በማድረግ ለመስኖ ልማት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አስረድተዋል። የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራው የአፈር ለምነት እንዲጨምር እና በጎርፍ ይጠረግ የነበረን ለም አፈር በማስቀረት የግብርና ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጉን አስረድተዋል። የአፈርና ውሃ እቀባ ሥራዎች በተከናወነባቸው ተፋሰሶች ላይ በክረምቱ ወራት ችግኞችን በመትከልና በመንከባበከብ ህብረተሰቡ በእንስሳት ማድለብ፣ በንብ ማነብ፣ በፍራፍሬ ልማት ተጠቃሚ እንዲሆን በቅንጅት መሰራቱንም አውስተዋል። በስራውም አርሶ አደሮች፣ ወጣቶችንና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች መሳተፋቸውን ጠቅሰዋል። የልማቱን ውጤታማነት ለማስቀጠልም በዘንድሮው የበጋ ወራት በ270 ተፋሰሶች ላይ የተለያዩ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች በጠንካራ የህዝብ ተሳትፎ ማከናወን ተችሏል ብለዋል ከተከናወኑ ተግባራት በዋናነት 54 ሺህ 693 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን የተለያዩ የእርከን ሥራዎች መሰራታቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል። ከዚህም በተጨማሪ ሰፋፊ የእርጥበት ማቆያ መዋቅሮችን ጨምሮ የተለያዩ ስነ-አካላዊ እና ስነ-ሕይወታዊ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን በስፋት መከናወናቸውን አቶ አብነት ጠቅሰዋል። የዞኑ አርሶ አደሮች የተፋሰስ ልማት ስራ ጠቀሜታውን በመረዳታችን በየዓመቱ ለአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራው ልዩ ትኩረት ሰጥተው መሳተፋቸውንም አንስተዋል። በአካባቢያቸው በተሠራው የተፈጥሮ ሀብት ሥራ ጎርፍን በመከላከልና የአፈር ለምነትን በመጠበቅ ለሰብል ምርታማነት ጉልህ አስተዋጾ እያደረገ መሆኑንም አመልክተዋል።
በግብርናው ዘርፍ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ቀጥሏል
Apr 17, 2026 113
ደዋጨፋ፤ሚያዚያ 9/2018(ኢዜአ)፡-የክልሉን ሰላም በማጽናት በግብርናው ዘርፍ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠሉን የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ ገለፁ። የፌዴራል፣ የአማራና የአፋር ክልሎች ከፍተኛ አመራሮች በኦሮሞ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ዳዋጨፋ ወረዳ በኩታ ገጠም የለማ የፍራፍሬ ችግኝ ተከላን ዛሬ አስጀምረዋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት፤ የክልሉን ሰላም በማጽናት የህብረተሰቡን ሁለተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በቅንጅት እየተሰራ ነው። በተለይም በግብርውና ዘርፍ ዘመናዊ ቴክኖሎጂንና የተሻሻለ አሰራርን በመተግበር የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር ለገበያ የሚተርፍ ምርት ለማምረት ሁሉን አቀፍ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በክልሉ አካበቢን መሰረት ያደረገ የልማት አቅጣጫ እየተተገበረ መሆኑን ጠቁመው ዛሬ የተጀመረው ኩታገጠም የፍራፍሬ ልማትም ይህንኑ ከግምት ያስገባ ነው ብለዋል። የተጀመረውን የፍራፍሬ ልማት ወደ አፋር ክልል አጎራባች ወረዳዎች በማስፋት ጥራት ያለው የፍራፍሬ ምርትን ከአገር ውስጥ አልፎ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሀጅ አወል አርባ በበኩላቸው የሁለቱን ክልል የህዝብ ለህዝብ ትስስር በልማትም አጠናክሮ ለማስቀጠል ቁርጠኛ አቋም ተወስዷል ብለዋል። በዚህም ዛሬ የተጀመረው የፍራፍሬ ልማት የሁለቱን ክልሎች አዋሳኝ ወረዳዎችን አካቶ በመተግበር የጋራ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችል እንደሆነም ገልፀዋል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን (ዶ/ር)፣ በሀገሪቱ ሁሉም ክልሎች ያለውን ፀጋና ሀብት በጥናት ለይቶ በማልማት ለሀገር ብልፅግና ለማዋል ጥረት እየተደረገ ነው ብለዋል። በግብርናው ዘርፍ በጥራት፣ በአይነትና በብዛት በማምረት ከፍጆታ አልፎ ለወጭ ንግድ የሚተርፍ አመራረት ላይ በማተኮር ውጤት እየተገኘ መሆኑንም ተናግረዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች እየታየ ያለው ኩታ ገጠም የፍራፍሬ ልማት ለአገር እድገትና ለህዝብ ተጠቃሚነት ድርሻው የጎላ እየሆነ መምጣቱን አስረድተዋል።
በደቡብ ኦሞ ዞን የበልግ ወቅት የችግኝ ተከላ ሥራ ተጀመረ
Apr 17, 2026 125
ዲመካ፣ ሚያዚያ 9/2018 (ኢዜአ)፡-በደቡብ ኦሞ ዞን በተያዘው የበልግ ወቅት ከ4 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያላቸው ሀገር በቀል ችግኞች ተከላ ሥራ መጀመሩን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ። በዞኑ የ2018 ዓ.ም የበልግ ወቅት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ችግኝ ተከላ ዛሬ በዲመካ ከተማ ተጀምሯል። የዞኑ ግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ምንላርገው አዲሱ በዚህ ወቅት እንደገለጹት በዞኑ በዘንድሮ የበልግ ወቅት ከ4 ሚሊዮን በላይ ዘርፈ ብዙ ጥቅም ያላቸው ሀገር በቀል ችግኞች ይተከላሉ። ህዝቡን በማሳተፍ ለሚከናወነው የችግኝ ተከላ መርሀግብር ከ2 ሚሊዮን በላይ የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ተዘጋጅተው ዛሬ የመትከል ሥራው በይፋ መጀመሩን ተናግረዋል። የችግኝ ተከላ ሥራው ከአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ ጎን ለጎን እንደሚካሄድ ገልጸው፣ ለግጦሽ ሣር የሚሆን ሥፍራን የመከለል ሥራም አብሮ ይከናወናል ብለዋል። እንደኃላፊው ገለጻ ዘንድሮ የሚተከሉት ችግኞች የአፈር መሸርሸርን ለመከላከል የሚያግዙ፣ ለምግብነት እና ለገቢ ምንጭነት የሚውሉ ፍራፍሬዎች እንዲሁም ለጥላነት የሚያገለግሉ ናቸው። በደቡብ ኦሞ ዞን ዲመካ ከተማ ዛሬ በተጀመረው የበልግ ወቅት የአረንጓዴ አሻራ መርሀሃ ግብር ችግኝ ተከላ ላይ የተሳተፉት አቶ ናደው ኤካደ በበኩላቸው በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ቀደም ሲል የተተከሉ ችግኞች ለተፈጥሮ አደጋ የነበራቸውን ተጋላጭነት እንደቀነሱላቸው ተናግረዋል። ልማቱ ያለውን ዘርፈ ብዙ ጥቅም በአግባቡ በመረዳታቸው በተያዘው የበልግ ወቅትም ሆነ በመጪው የክረምት ወቅት በሚካሄድ የተከላ መርሀግብር የሚያደርጉትን ተሳትፎ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች እና የአረንጓዴ አሻራ ንቅናቄዎች ተጨባጭ ውጤት እንዳመጡ የጠቀሱት ደግሞ አቶ ስጦታው አመዴ ናቸው። የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች በተሰሩባቸው አካባቢዎች ተጨባጭ ለውጦች እንደመጡ ገልጸው፣ በተለይ ተራቁተው በነበሩ አካባቢዎች ችግኝ በመተከሉ እያገገሙ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ለኮፕ 32 ብሔራዊ ኮሚቴ አቋቁማ የዝግጅት ስራዎችን እያከናወነች ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Apr 17, 2026 189
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ለኮፕ 32 ብሔራዊ ኮሚቴ አቋቁማ የዝግጅት ስራዎችን እያከናወነች እንደምትገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት የኮፕ 32 አስተናጋጅ እንደሆነ ሀገር፤ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ኮሚቴ በይፋ በማቋቋም ዝግጅቷን ቀደም ብላ ጀምራለች ብለዋል። ሂደቱን በግልጽ ግብ እና በላቀ ምልከታ ለመምራት ቁልፍ አመራር መመደቡና የኮፕ ፕሬዝደንት መዋቅርም የተቀናጀና የላቀ ውጤት የሚያስገኙ የቅድሚያ ተግባራቱን መጀመሩን ገልጸዋል። ዛሬ ከብሔራዊ ኮሚቴው ጋር በነበራቸው ስብሰባ በተለያዩ ዘርፎች የተከናወኑ ሥራዎችን በመገምገም ክፍተቶችን የመለየት እና ጥረቶች ከሀገራዊ ርዕይ ጋር የተጣጣሙ መሆናቸው መዳሰሱን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በመድረኩ የጋራ ቀጣይ አቅጣጫ መቀመጡን ጠቁመው፤ ትኩረቱም በጠንካራ ትብብር፣ በተዋሃደ ታላቅ ርዕይ እና በጋራ ጽኑ ትጋት ተናቦ ይህን ዓለም አቀፍ ሁነት በልህቀት በማስተናገድ የሀገርን ታላቅነት ዳግም ማሳየት መሆኑን አስታውቀዋል።
በክልሉ ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በዝግጅት ላይ ከሚገኙ ችግኞች መካከል 70 በመቶው የፍራፍሬ ችግኞች ናቸው
Apr 17, 2026 188
በጋምቤላ ፤ ሚያዝያ 9/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ልማት እየተዘጋጁ ከሚገኙት ችግኞች መካከል 70 ከመቶ የሚሆኑት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡ በክልሉ ለመጪው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር በ70 የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እየተዘጋጁ እንደሆነ ቢሮው ገልጿል። በቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ ኬት ቾል ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚያግዙና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ላላቸው ችግኞች ትኩረት ተሰጥቷል። በዚህም 70 በሚሆኑ የግልና የመንግስት የችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እየተዘጋጁ ከሚገኙት ችግኞች መካከል 70 ከመቶ የሚሆኑት ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን ተናግረዋል። ከችግኞቹ መካከል ማንጎ፣ አቮካዶ፣ ፓፓያ ፣ ዘይቱናና ሎሚ ዋነኞቹ እንደሆኑም ገልጸዋል። ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ ልማት እየተዘጋጁ ካሉት የፍራፍሬ ችግኞች ባለፈ ከአካባቢው የአየር ንብረት ጋር የሚጣጣሙ የደን ችግኞች እየተዘጋጁ መሆናቸውንም ጠቁመዋል፡፡ በበጋው ወራት የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎች የተከናወነባቸው ከዘጠኝ ሺህ ሄክታር በላይ የተራቆቱ አካባቢዎችን ስነ-ህይወት ለማልበስ የመረጣና የቦታ ልየታ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም ገልጸዋል። በክልሉ ባለፉት ተከታታይ ዓመታት በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የተተከሉት የፍራፍሬና ሌሎች ችግኞች የአካባቢውን ስነ-ምህዳር ከመቀየር ባለፈ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በማገዝ ረገድ የጎላ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙም ተናግረዋል። በቀጣይም በክረምቱ ለሚከናወነው የአረንጓዴ አሻራ ልማት የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በሚያግዙ ችግኞች ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝ ዳይሬክተሩ ተናግረዋል።
በክልሉ የህብረተሰቡ ችግኝ የመትከል ባህል እያደገ መጥቷል
Apr 16, 2026 161
ዋጂፎ፤ሚያዝያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የህብረተሰቡ ችግኝ የመትከል ባህል እያደገ መምጣቱን የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) ገለጹ። በክልሉ ጋሞ ዞን የ2018 ዓ.ም የበልግ ወቅት የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ ግብር "አረንጓዴ አሻራ ለተምሳሌት ሀገር" በሚል መሪ ሃሳብ ዛሬ በምዕራብ አባያ ወረዳ ዋጂፎ ከተማ ተካሂዷል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የሥራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ አበባየሁ ታደሰ (ዶ/ር) እንደገለጹት፣ በአየር ንብረት ለውጥ የሚከሰተውን የተፈጥሮ አደጋ በዘላቂነት ለመቋቋም ለችግኝ ተከላ ልዩ ትኩረት ተሰጥቷል። የለውጡ መንግስት በአየር ንብረት ለውጥ የሚከሰትን ችግር መቋቋም እንዲቻል ለአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የተተከሉ ችግኞች የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እያገዙ መሆኑን ጠቀመው፣ በክልሉ ህብረተሰቡ ችግኝ የመትከልና አካባቢውን የመንከባከብ ሥራ ባህሉ እያደረገ መምጣቱን ተናግረዋል። የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አደጋ ለመከላከል ችግኝ ተከላን የዘወትር ተግባር ማድረግ እንደሚገባ ያሳሰቡት አበባየሁ (ዶ/ር)፣ ችግኝ ተከላው ለግብርና ምርታማነት፣ ለሥራ ዕድል ፈጠራና ገቢን ለማሳደግ እያገዘ መሆኑን አስረድተዋል። ልማትን በዘላቂነት ለማረጋገጥ በአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር የሚከናወነውን የልማት ሥራ ማጠናከር ይገባል ያሉት ደግሞ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊና የዲላ ክላስተር አስተባባሪ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) ናቸው። መርሀ ግብሩ ለምግብ ዋስትና፣ ለዘላቂ ልማት፣ ለኢንዱስትሪ ሽግግር እንዲሁም ለምግብ ሉዓላዊነት መረጋገጥ የማይተካ ሚና ይጫወታል ብለዋል። በመሆኑም ዘንድሮ በክልሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች እንደሚተከሉ የጠቀሱት መሪሁን (ዶ/ር)፣ ግብርናን በማዘመን የምግብ ሉዓላዊነትን በአጭር ጊዜ ውስጥ ለማረጋገጥ እንደሚሰራም ተናግረዋል። የጋሞ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ደምስ አድማሱ (ዶ/ር) በበኩላቸው እንዳሉት፣ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ በዜጎች ሕይወት ላይ ተጨባጭ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ተናግረዋል። በዘንድሮ የበልግ ወቅት በሚከናወን የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ከዘጠኝ ሚሊዮን በላይ የፍራፍሬ ችግኞችን ለመትከል አስፈላጊው ቅድመ ዝግጅት በማድረግ ወደ ትግበራ መገባቱን አንስተዋል። በተለይ በዞኑ በተደጋጋሚ የሚከሰቱ የጎርፍ እና የመሬት መንሸራተት አደጋዎች ተፈጥሮን በአግባቡ ባለመንከባከብ የሚከሰቱ መሆናቸውን ጠቁመው፣ ለችግኝ ተከላው ልዩ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። በምዕራብ አባያ ወረዳ የዋጂፎ ከተማ ነዋሪ የሆኑት ሃምሳ አለቃ ዋጋሶ ኦቼ እና አቶ ዳንኤል ዳንጋሮ በበኩላቸው ቀደም ሲል በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የተተከሉ ችግኞች በአካባቢያቸው ተጨባጭ ውጤት ማምጣታቸውን ተናግረዋል። በየዓመቱ በተተከሉ ችግኞች ቀደም ሲል ሞቃት የነበረው የአካባቢው የዓየር ጸባይ እየተስተካከለ መምጣቱን የገለጹት ነዋሪዎቹ፣ በግብርና ሥራም ተጨባጭ ውጤት እየታየ መሆኑን ተናግረዋል። ለዚህም በመርሀ ግብሩ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸውን ፍራፍሬዎች በማልማት ተጨማሪ ገቢ ከማግኘት ባለፈ፣ ለጓሮ አትክልትና ለእንስሳት መኖ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ይህን ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ በዛሬው የችግኝ ተከላ መርሀግብር መሳተፋቸውን ገልጸው፣ በቀጣይም በችግኝ ተከላና እንክብካቤ የሚያደርጉትን አስተዋጽኦ እንደሚያጠናክሩ አረጋግጠዋል። በችግኝ ተከላ መርሃ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ እንዲሁም የከተማ አስተዳደር የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተሳትፈዋል።
በሶማሌ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የችግኝ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Apr 16, 2026 148
ጅግጅጋ፣ ሚያዝያ 8/2018(ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል ለዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የችግኝ ዝግጅት እየተደረገ ነው፡፡ በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የተተከሉ ችግኞች የአካባቢን ስነምህዳር ከመቀየር ባለፈ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ በመስጠት ላይ መሆናቸው ይታወቃል። በሶማሌ ክልል አከባቢ ጥበቃና ገጠር መሬት አስተዳደር ቢሮ የደን ልማት ዳይሬክተር ሂቦ ኑር ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በለውጡ ዓመታት በክልሉ በአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር በተከናወኑት የችግኝ ተከላ ተግባራት መሬት መራቆትና የአፈር መሸርሸርን መከላከል እየተቻለ ነው። በክልሉ በመርሃ ግብሩ የተተከሉት ችግኞች የአፈር መሸርሸርና የመሬት መራቆት በመከላከልና የአየር ንብረት ተጽዕኖ ለመቋቋም አበረታች ለውጥ ያመጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዘንድሮው ክረምት የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርም በክልሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ለመትከል ታቅዶ የችግኝ ዝግጅት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ የታቀደውን የችግኝ ተከላ መርሃግብር ለማሳካት በ160 የግልና የመንግስት ችግኝ ጣቢያዎች ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆናቸውንም ተናግረዋል። ችግኞቹ ለማህበረሰቡ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን የሚሰጡ፣ ለምግብነት የሚውሉ የፍራፍሬ ዓይነቶች፣ ለደንነት የሚውሉ፣ ለውበትና ለእንስሳት መኖ የሚሆኑ መሆናቸውን ተናግረዋል። ህብረተሰቡም የሚተከሉ ችግኞችን በመከታተልና አስፈላጊውን እንክብካቤ በማድረግ የደን ሽፋን ለመጨመር የበኩሉን እንዲወጣ ዳይሬክተሩ አስገንዝበዋል።