ቀጥታ፡
አካባቢ ጥበቃ
ለ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የላቀ ሀገራዊ ራዕይን በሚያሳካ መልኩ ዝግጅት እየተደረገ ነው
Mar 15, 2026 152
አዲስ አበባ፤መጋቢት 6/2018 (ኢዜአ)፡-ለ2018 ዓ.ም የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የላቀ ሀገራዊ ራዕይን በሚያሳካ መልኩ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተጀመረ ሲሆን፤ መርሃ ግብሩ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞች ተተክሏል፡፡ በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሀብት ልማት፣ ጥበቃና አጠቃቀም መሪ ሥራ አስፈፃሚ ፋኖሴ መኮንን ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለዘንድሮው መርሃ ግብር የመጀመሪያ ዙር የችግኝ ዝግጅት ተጠናቋል። ለስኬታማነቱም በርካታ ቁልፍ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመው፤ ሰባት ነጥብ አምስት ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል የሚያስችል ዕቅድ መዘጋጀቱን አብራርተዋል። በዚህም እስካሁን ከስድስት ቢሊዮን በላይ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ከችግኞቹ መካከልም 40 በመቶው ሀገር በቀል የደን ችግኞች ሲሆኑ፤ ቀሪው 60 በመቶው ደግሞ እንደ ፍራፍሬ እና የእንስሳት መኖ ያሉ ዘርፈ ብዙ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ያላቸው ናቸው ብለዋል። በአሁኑ ወቅት በሀገር አቀፍ ደረጃ 110 ሺህ የችግኝ ጣቢያዎች ወደ ሥራ መግባታቸውን ጠቁመዋል፡፡ የዘንድሮው የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሐ ግብር በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ መሆኑ ጠቅሰው፤ ከሰባት ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆን የመሬት ይዞታ በዲጂታል ጂኦ-ሪፈረንስ ክትትል የሚደረግበት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በተለይም በአንድ ጀምበር በሚከናወነው ተከላ ላይ የቴክኖሎጂው አጠቃቀም ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ይደረጋል ብለዋል፡፡ መርሃ ግብሩ በርካታ ትልልቅ ግቦችን ያነገበ ሲሆን፤ የአየር ንብረት ለውጥን መከላከል፣ የምግብ ዋስትና፤ ኢኮኖሚና ቀጣናዊ ትስስርን ማጠናከር ዋነኞቹ ናቸው ብለዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ብቻ ሳይሆን የሥራ ዕድል ፈጠራን፣ የተፋሰስ ልማትን እና የአፈርና ውሃ ጥበቃን ያካተተ ሁለንተናዊ የልማት ስትራቴጂ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስኬት በምሳሌነት የሚወሰድ ነው
Mar 14, 2026 105
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስኬት በምሳሌነት የሚወሰድ የልማት አጀንዳ መሆኑን በኢትዮጵያ የሕንድ አምባሳደር አኒል ኩመር ራይ ገለጹ። አምባሳደር አኒል ኩመር ራይ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ፤ የኢትዮጵያ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በርካታ ችግኞችን በመትከል የካርቦን ልቀትን መቀነስ የሚያስችል ውጤት እያስገኘ መሆኑን ገልጸዋል። ከብክለት ነፃ የሆኑ የትራንስፖርት አማራጮችን በማስፋት በኩልም ለአየር ንብረት ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ የኢኮኖሚ መገንባት የሚያስችል ወሳኝ እርምጃ እየወሰደች እንደምተገኝም አንስተዋል። የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስኬት በምሳሌነት የሚወሰድ የልማት አጀንዳ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የኢኮኖሚ ሥርዓት ግንባታም ለሌሎች የአፍሪካ እና የዓለም ሀገራት ተሞክሮ የሚወሰድበት መሆኑን ገልጸዋል። ሕንድም ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ሥርዓት ለመገንባት በምታደርገው ጥረት ትብብሯን አጠናክራ እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል። በቅርቡ ለአንድ ጊዜ አገልግሎት የሚሰጡ የፕላስቲክ መያዣዎች ላይ የእግድ ውሳኔ መተላለፉ ለአካባቢ ደኅንነትና ሥነ-ምኅዳር ጥበቃ ጉልህ ፋይዳ ያለው ወሳኝ እርምጃ መሆኑን አንስተዋል። በቀጣይም ሕንድ በአካባቢ ጥበቃና አረንጓዴ ኢኮኖሚ ሥርዓት ያላትን ልምድና ተሞክሮ በማጋራት ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ሁለንተናዊ ትብብር አጠናክራ እንደምትቀጥል ገልጸዋል።
አዋጁ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግብ ለማድረስ ያግዛል
Mar 13, 2026 228
አሶሳ፤ መጋቢት 4/2018(ኢዜአ)፦የተሻሻለው የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ አዋጅ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግብ ለማድረስ እንደሚያግዝ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አካባቢና ደን ጥበቃ እና አየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን አስታወቀ። በክልሉ ህብረተሰቡ በፕላስቲክ ከረጢት ምትክ አማራጭ ምርቶችን በስፋት እንዲጠቀም እየተደረገ መሆኑም ተመላክቷል፡፡ የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሉቅማን አብዱልቃድር እንዳስታወቁት፤ የተሻሻለውን የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ አዋጅ በክልሉ ተግባራዊ ለማድረግ በተለያዩ መድረኮች ህብረተሰቡ ግንዛቤ እንዲኖረው ተደርጓል። በዚህም በፕላስቲክ ምርት ንግድ ላይ የተሰማሩ ግለሰቦች አማራጭ ምርቶችን ማምረት እንዲጀምሩ በተግባር የታገዘ የሙያ ስልጠና እንዲያገኙ መደረጉን ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። በአሁኑ ሰዓት የተወሰኑ ግለሰቦች ተኪ ምርቶችን ማዘጋጀት መጀመራቸውን ጠቁመው፥ በዘርፉ ላይ ለሚሰማሩ አካላት አስፈላጊው ድጋፍ እንደሚደረግ ተናግረዋል።   የፕላስቲክ ከረጢቶች ለአካባቢ ብክለት መንስኤ መሆናቸውን የገለፁት አቶ ሉቅማን አዋጁ እንደ ሀገር የተጀመረውን የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ ከግብ ለማድረስ ያግዛል ብለዋል። አዋጁን ተከትሎ የፕላስቲክ ከረጢቶችን የሚተኩ ምርቶች ላይ የተሰማራችው ወጣት ጅራቱ ሰንበቶ በበኩሏ፤ አዋጁን ተግባራዊ ለማድረግ የህብረተሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ ይገባል ብላለች። በቅርቡ ወደ ስራ መግባቷን ገልጻ አዲስ አበባ በመሄድ ሙያዊ ስልጠና መውሰዷን ተናግራለች።   በአሁኑ ሰዓት ሌሎች በዘርፉ የሚሰማሩ የስራ ዕድል ተጠቃሚዎችን ለማሰልጠን ፍላጎት እንዳላት ገልጻ ጎን ለጎንም ለንግድ ተቋማት የወረቀት ከረጢቶችን በማዘጋጀት የማስተዋወቅ ስራ እያከናወነች መሆኑን ተናግራለች። አዋጁን ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ በማድረግ የፕላስቲክ ከረጢቶች የሚያደርሱትን የአካባቢ ብክለትና በህብረተሰቡ ላይ የሚያስከትሉትን የጤና ጠንቅ መከላከል እንደሚገባም ነው የገለጸችው።
በበልግ ዝናብ ተጠቃሚና ሰብል አብቃይ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚኖረው የዝናብ ሁኔታ ለግብርና ስራ አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል 
Mar 12, 2026 128
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 3/2018(ኢዜአ)፦ በቀጣዮቹ አስር ቀናት በበልግ ዝናብ ተጠቃሚና ሰብል አብቃይ የሀገሪቱ አካባቢዎች የሚኖረው የዝናብ ሁኔታ ለግብርና ስራ አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለፀ። ኢንስቲትዩቱ ከመጋቢት 2 እስከ መጋቢት 11 ቀን 2018 ዓ.ም የሚኖረውን የአየር ሁኔታ አዝማሚ አስመልክቶ ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው፤ በቀጣዮቹ አስር ቀናት ለዝናብ ምቹ ሁኔታን የሚፈጥሩ የሚቲዎሮሎጂ ገፅታዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ። ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን የልማት እቅዷ አካል በማድረግ በአካባቢ ጥበቃ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች ትገኛለች በልግ ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑት በደቡብ እና በደቡብ ምስራቅ፣ የስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎች፣ የመካከለኛው የሀገሪቱ አካባቢዎች እንዲሁም በደቡብ ምዕራብ ላይ የተሻለ ገፅታ እንደሚኖራቸው ይጠበቃል። በዚህም በደቡብ፣ መካከለኛው፣ ምስራቅና እና ሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ ይጠበቃል። እነዚህ አካባቢዎች በጥቂት ስፍራዎቻቸው ላይ ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚያገኙ የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ። በዚህም መሰረት ወላይታ፣ ጎፋ፣ ጌዴዮ፣ ጋሞ፣ ባስኬቶ፣ አሪ፣ ኮንሶ፣ ቡርጂ፣ አሌ፣ ጋርዱላ፣ ኮሬ እና ደቡብ ኦሞ ዞኖች እንዲሁም ሁሉም የሲዳማ ክልል ዞኖች ከመካከለኛ እስከ ከባድ የዝናብ መጠን ያገኛሉ ብሏል ኢንስቲትዩቱ። ይህ የዝናብ መጠን በቂ የአፈር እርጥበት እንዲኖር፣ የሰብሎች የውሃ ፍላጎት መሟላት፣ ለቋሚ ተክሎች እድገትና የግጦሽ ሳርና የመጠጥ ውሃ አቅርቦት መሻሻል እንዲኖር በማድረግ ለግብርና ሥራ አዎንታዊ ሚና እንዳለው ጠቅሷል። የአፈር መሸርሸር፣ በሰብል ማሳ ላይ ውሃ መተኛት፣ የሰብል በሽታና ተባይ እንዲሁም የአረም መከሰት ሊያስከትል እንደሚችልም አስጠንቅቋል። ስለሆነም የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችን መስራት፣ የሰብል በሽታንና አረም እንዳይስፋፋ መከላከል፣ የሰብል ማሳዎችን በቅርበት መከታተልና የአየር ጠባይ ትንበያና ምክረ ሃሳቦችን ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል። በመሆኑም የአየር ሁኔታው አስተዋፅኦ በላቀ ሁኔታ ለመጠቀምና ሊከሰት የሚችለውን አሉታዊ ተጽዕኖ ለመቀነስ የሚቲዎሮሎጂ ምክረ ሀሳቦችን ከወዲሁ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚያስፈልግ አስረድቷል። በሌላ በኩል በጋምቤላ፣ በአፋር፣ በሶማሌ፣ በቤንሻንጉል-ጉሙዝና በምዕራብ አማራ አካባቢዎች ቀን ላይ ከፍተኛ የሙቀት መጠን እንዲሁም ሌሊት ላይ ወበቅ እንደሚጠበቅ ገልጿል።
በጉጂ ዞን ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን በዘላቂነት ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Mar 11, 2026 107
ነጌሌ ቦረና ፤ መጋቢት 2/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በዘንድሮው ዓመት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን በዘላቂነት ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በኦሮሚያ ክልል የተሻሻሉና የአካባቢን ስነ-ምህዳር ታሳቢ ያደረጉ የቡና ችግኞች ይተከላሉ በጽህፈት ቤቱ የተፈጥሮ ሀብት ቡድን መሪ አቶ ወንዶ ሸርቦቴ ለኢዜአ እንዳሉት፤በዘንድሮ የክረምት ወቅት ለሚካሔደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም የሚያስችሉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው። የችግኝ ዝግጅቱ በዞኑ ባሉ ከ170 በላይ ችግኝ ማፍያ ጣቢያዎች እየተካሔደ ሲሆን እስካሁን ባለው ሒደት 89 ነጥብ 3 ሚሊዮን ችግኞችን ለማዘጋጀት መቻሉን አስታውቀዋል።   ይህም በየዓመቱ የሚከሰተውን ድርቅና የአካባቢ መራቆት ችግርን በዘላቂነት ለመቋቋም እንደሚያስችል ታምኖበታል ነው ያሉት። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር አካል የሆነው የችግኝ ዝግጅቱ የጉጂ ዞንን ደጋ፣ ወይና ደጋና ቆላማ የአየር ንብረት ታሳቢ ያደረገ መሆኑን አውስተዋል። ለተከላ ከተዘጋጁት የችግኝ ዝርያዎች ውስጥ ጽድ፣ ግራቪሊያ፣ ወይራ፣ ዋንዛ፣ ዝግባና ሌሎችም እንደሚገኙበት ነው ያመለከቱት። እንዲሁም ለከተማ ውበት፣ ለእንስሳት መኖ፣ ለምግብነት የሚውሉና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ያላቸው እንደ አቮካዶ፣ ማንጎ፣ ሙዝና ግሽጣ ያሉ ፍራፍሬዎችን ያካተተ የችግኝ ዝግጅት መደረጉን አስረድተዋል። ችግኞቹን ለማልማትና ለውጤት ለማብቃት ከሰውና ከእንስሳት የተከለለ ከ21 ሺህ 340 ሄክታር በላይ መሬት መዘጋጀቱን አስረድተዋል።   በመጪው ክረምት በሚካሄደው የችግኝ ተከላ ስራ ከ205 ሺህ በላይ ህዝብ ለማሳተፍ የቅስቀሳና የግንዛቤ ማሳደግ ስራ እየተካሄደ እንደሚገኝም አመላክተዋል። በዞኑ ባለፈው ዓመት ከተተከሉት ችግኞች በህዝብ እንክብካቤና ጥበቃ 83 በመቶው መጽደቁን በመስክ ምልከታና ክትትል ለማረጋገጥ ተችሏል ብለዋል።
በክልሉ በበልግ ወቅት እየጣለ ባለው ዝናብ ጎርፍን ጨምሮ የመሬት መንሸራተት አደጋ እያጋጠመ በመሆኑ አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግ ኮሚሽኑ አሳሰበ
Mar 10, 2026 163
አርባምንጭ ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የበልግ ወቅትን ተከትሎ እየጣለ ባለው ዝናብ ጎርፍን ጨምሮ የመሬት መንሸራተት አደጋ እያጋጠመ በመሆኑ ህብረተሰቡ አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርግ እንደሚገባ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራርና የምግብ ዋስትና ኮሚሽን አሳሰበ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አደጋ ስጋት ስራ አመራርና የምግብ ዋስትና ኮሚሽን ኮሚሽነር ወገኔ ብዙነህ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የበልግ ወቅትን ተከትሎ እየጣለ ያለው ዝናብ በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ የጎርፍና የመሬት መንሸራተት አደጋ እያስከተለ ነው።   በክልሉ በጋሞ፣ በወላይታ፣ በደቡብ ኦሞ፣ በኮንሶ፣ በጌዲኦ እና በጎፋ ዞኖች በሚገኙ ተራራማ አካባቢዎች ያልተጠበቀ የመሬት መንሸራተት እንዲሁም በአንዳንድ ቆላማ አካባቢዎች ደግሞ የጎርፍ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል አመላክተዋል። ስለሆነም ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች የሚኖሩ የክልሉ ነዋሪዎች አስፈላጊውን ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባ አሳስበዋል። ህብረተሰቡ በየአካባቢው አጠራጣሪ የሆኑ የመሬት መሰንጠቆች፣ የውሃ ምንጮችና ሌሎች ለውጦች ሲከሰቱ በፍጥነት ለሚመለከተው ክፍል መረጃ በመስጠት ብሎም ስጋት ወደሌለባቸው አካባቢዎች በመሄድ ራሱን ከአደጋው እንዲጠብቅ አስገንዝበዋል። ኮሚሽነር ወገኔ አክለውም በክልሉ የተፈጥሮ አደጋዎችን በዘላቂነት ለመከላከልም በአረንጓዴ አሻራና የተፋሰስ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑንም አስረድተዋል። ከዚህ ቀደም በክልሉ በተለያዩ ዞኖች በተፈጥሮ አደጋ ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን ስጋት ወደሌለባቸው አካባቢዎች በማስፈር መልሶ የማቋቋም ስራ ሲከናወን መቆየቱን አስታውሰዋል። ችግሩን በሳይንሳዊ መንገድ በዘላቂነት ለመከላከል በጥናት ላይ የተመሰረተ ስራ እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል።   የጋሞ ዞን አደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መስፍና ማኑቆ በበኩላቸው፤ ትናንት ምሽት በጣለው ከፍተኛ ዝናብ በዞኑ ቦንኬ እና ጋጮ ባባ ወረዳዎች በመሬት መንሸራተት አደጋ የሰው ህይወት ማለፉን ገልጸዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ እና ዙሪያ ወረዳ የኩልፎ እና የሴጎ ወንዞች ሙላት ባስከተሉት የጎርፍ አደጋ በተለያዩ ተቋማትና መሠረተ ልማት ላይ ጉዳት ማድረሱን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የአደጋው መጠን እየተጣራ መሆኑን ጠቁመው ከቤት ንብረታቸው የተፈናቀሉ ወገኖችን መልሶ ለማቋቋም ከነዋሪዎች፣ ከግብረ-ሰናይ ድርጅቶችና ከባለሀብቶች ጋር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን የልማት እቅዷ አካል በማድረግ በአካባቢ ጥበቃ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች ትገኛለች
Mar 10, 2026 148
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የሰርኩላር ኢኮኖሚን በሀገራዊ የልማት እቅዷ ውስጥ በማካተት በአካባቢ ጥበቃ ረገድ ለአፍሪካ አርዓያ የሚሆን ተግባር እያከናወነች መሆኗን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ገለፁ። የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ከህንድ የሳይንስና አካባቢ ማዕከል ጋር በመተባበር ያዘጋጁት በሰርኩላር ኢኮኖሚ ላይ የሚያተኩረው 8ኛው የከተሞች ፎረም ከመጋቢት 1 እስከ 3 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) በፎረሙ መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት፣ የሰርኩላር ኢኮኖሚ መርህ የአየር ንብረት የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ እና የ10 ዓመቱ የልማት እቅድ አካል ነው። ስትራቴጂው የኢኮኖሚ እድገትን ከአካባቢ ጥበቃ ጋር ማስተሳሰር፣ ዘላቂ የቆሻሻ አያያዝን እና መልሶ ጥቅም ላይ ማዋልን ማጠናከር እንዲሁም በአረንጓዴ ስራ ፈጠራ በተለይም ወጣቶችንና ሴቶችን ተጠቃሚ ማድረግ ላይ ያለመ ነው ብለዋል።   በተጨማሪም በግብርና፣ በምግብ ስርዓት እና በግንባታ ዘርፎች ላይ ያተኮረ ብሄራዊ የሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ-ካርታ ወደ ትግበራ መሸጋገሩን ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮጵያ ለምርምር፣ ለቴክኖሎጂ ሽግግር እና ለግል ዘርፉ ተሳትፎ ማዕከል የሚሆን "የሰርኩላር ኢኮኖሚ የልህቀት ማዕከል" በአዲስ አበባ የማቋቋም ሂደት መጀመሯን ገልጸዋል፡፡ ማዕከሉ የሀብት ምርታማነትን በማሳደግ እና በመላው አፍሪካ የአጋርነት ትስስርን በመፍጠር ረገድ ወሳኝ ሚና እንደሚኖረውም ጠቅሰዋል፡፡ የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፋንታ ደጀን በበኩላቸው በኢትዮጵያ የከተማ ልማት ስራዎች ከአካባቢ ጥበቃ ጋር ተሰናስለው እየተሰሩ መሆኑን ገልጸዋል።   የሰርኩላር ኢኮኖሚ ከተሞች ሀብትን በብክነት ፈንታ ወደ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እንዲቀይሩ የሚያስችል ማዕቀፍ መሆኑን አስገንዝበዋል። በኢትዮጵያ የህንድ አምባሳደር አኒል ኩመር ራይ በአፍሪካ እየታየ ላለው ፈጣን የከተሞች መስፋፋት ተስማሚ የአካባቢ ጥበቃ መፍትሄዎች እንደሚያስፈልጉ ገልጸዋል።   በዚህም ኢትዮጵያ በኮሪደር ልማት እያከናወነች ያለው ተግባር ለሌሎች ሀገራት ትልቅ ትምህርት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መሪነት የተከናወኑ የልማት ስራዎች ከተማን እንዴት መለወጥ እንደሚቻል በተግባር ማሳየት መቻሉን ጠቅሰው አዲስ አበባ አሁን ላይ ሰፋፊ መንገዶች፣ የብስክሌት መጓዣያዎች እና አረንጓዴ ስፍራዎች ያሏት ዘመናዊ ከተማ መሆኗን ጠቁመዋል፡፡
የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር አስችለዋል
Mar 9, 2026 182
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30 /2018(ኢዜአ)፦የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች ጤናማ የአካባቢ ሥነ-ምኅዳር መፍጠር ማስቻላቸውን የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ገለጸ። የኢትዮጵያ የአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ተምሳሌታዊ ተግባር ነው የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ሌሊሴ ነሜ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንዳሉት፤ በሁለተኛው ዙር ፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ በአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ ፈጠራና የሕግ ተከባሪነት ስኬታማ ስራ ተሰርቷል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶችም የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ለፅዱ ኢትዮጵያ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ መሆኑን ገልጸዋል። የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የፕላስቲክ፣ የአፈር፣ የውሃ፣ የአየርና የድምፅ ብክለትን በመከላከል የአካባቢና ማህበራዊ ተፅዕኖ ግምገማ ላይ ትኩረት ማድረጉን ተናግረዋል። በንቅናቄው መሠረት በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ15 ሚሊየን በላይ ከሚሆን ህዝብ ጋር የገፅ ለገፅ መድረክ በመፍጠር የአካባቢ ጥበቃና ፅዱ አካባቢ የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርት መሰጠቱን አንስተዋል። በመገናኛ ብዙሃንም ከ50 ሚሊየን በላይ ህዝብ ተደራሽ በማድረግ ህብረተሰቡ በአካባቢ ላይ የሚደርስ ብክለትን መቀነስ የሚያስችል የዕውቀት፤ የግንዛቤና የሕግ ማስከበር ሥራ መሰራቱን አስረድተዋል። በዚህም በሁለት ዙር የፅዱ ኢትዮጵያ ንቅናቄ የዜጎችን የአካባቢ ጥበቃ ግንዛቤ በማሳደግ ፅዱና የበለፀገች ኢትዮጵያን ለትውልድ ማስተላለፍ የሚያስችል መሰረት መጣሉን ጠቅሰዋል። በቀጣይም 3ኛ ዙር የፅዱ ኢትዮጵያን ባህል እናድርግ ሀገር አቀፍ ንቅናቄ ለማስጀመር ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። በ3ኛው ዙር ሀገር አቀፍ ንቅናቄም የለውጡን ዓመታትን የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የከተማና ገጠር ኮሪደር ልማት ስኬቶች በማጽናት ባህል ይሰራል ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት የተተገበሩ የአረንጓዴ አሻራ፣ የወንዝ ዳርቻ፣ የገጠርና ከተማ ኮሪደር ልማት ስኬቶች የአካባቢ ብክለትን በመቀነስ ለፅዱ ኢትዮጵያ ግንባታ ወሳኝ ሚና እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል። የኮሪደር ልማት ስራ የፍሳሽ አወጋገድና የቆሻሻ አያያዝን በማዘመን ዜጎችን ፅዱ የመኖሪያ ምኅዳር በማጎናጸፍ የወንዞችን ጤናማነት የሚያስጠብቅ ተምሳሌታዊ የልማት ስኬት መሆኑንም ተናግረዋል። በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚከናወኑ የአፈርና ውሃ ጥበቃና የእርከን ሥራ የሥነ-ምኅዳር ደኅንነትን በማስጠበቅ ገንቢ ሚና እየተወጣ እንደሚገኝ አንስተዋል። በሰርኩላር ኢኮኖሚ ፍኖተ ካርታም ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል የሚሰሩ የግሉን ዘርፍ ማበረታታት የሚያስችሉ ሥራዎች እየተሰሩ መሆኑንም አመላክተዋል።
‎በጋምቤላ ክልል የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ 
Mar 9, 2026 209
ጋምቤላ ፤ የካቲት 30 /2018(ኢዜአ)፦በጋምቤላ ክልል የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ አለሚቱ ኡሞድ ገለፁ። በክልሉ ኮንትሮባንድ እና ህገ-ወጥ የንግድ እንቅስቃሴን በመከላከል ጤናማ የገበያ ሥርአት ለመፍጠር ትኩረት ተሰጥቷል ‎‎በክልሉ በዘንድሮው ዓመት እየተካሄደ ባለው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማትና የተፈጥሮ ሃብት ጥበቃ ስራዎች የማጠናከሪያ መርሃ ግብር በጎግ ወረዳ እየተካሔደ ነው። ‎‎ርዕሰ መስተዳደሯ አለሚቱ ኡሞድ በዚሁ ወቅት እንዳሉት ፤የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የጎላ ድርሻ አላቸው።   ‎‎ይህን ታሳቢ በማድረግ በተራቆቱ አካባቢዎች የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራዎችን በማጠናከር በክልሉ የተጀመረውን የግብርና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ስኬታማ ለማድረግ በትኩረት መስራቱ ይቀጥላል ብለዋል። ‎በክልሉ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የተፋሰስ ልማትና የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብር የአካባቢ መራቆትንና የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል በኩል እመርታዊ ለውጥ እንዲመጣ እያስቻለ መሆኑን ገልጸዋል። ‎‎በመሆኑም የተጀመረው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራ በሁሉም አካባቢዎች ተጠናክሮ እንዲቀጥል አመራሩ በቁርጠኝነት መስራት ይገባዋል ብለዋል። ‎በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት ‎የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፕሮፌሰር እያሱ ኤልያስ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ እንደ ሀገር የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመላቀቅ ለተቀመጠው ግብ መሳካት የተፈጥሮ ሃብት ልማት ስራዎች የላቀ አበርክቶ አላቸው።   ‎‎ባለፉት አመታት ለተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ ስራዎች በተሰጠው ትኩረት የተጎዱ መሬቶች እንዲያገግሙና የግብርና ምርታማነት እንዲጨምር ማስቻሉን ተናግረዋል። ‎‎በመሆኑም የተፈጥሮ ሃብትን መሠረት ያደረገ የግብርና ልማትን ለማስፋት የተጀመረው ጥረት በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። ‎‎የጋምቤላ ክልልም ለግብርና ልማት የተመቸ ስነ ምህዳር ያለው አካባቢ መሆኑን ጠቅሰው ይህንን ሃብት በአግባቡ አልምቶ ከመጠቀም አንፃር የቅንጅት ስራዎች እንደሚጠናከሩ ገልፀዋል። ‎በክልሉ ሲከናወን በቆየው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ስራ የአፈር እርጥበታማነትንና ለምነትን በማሻሻል የሰብል ምርታማነትን እያሳደገ ይገኛል ያሉት ደግሞ የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንድሮው ቱት ናቸው። ‎‎በክልሉ የተፋሰስ ልማትን በማጠናከር የከርሰ ምድርና የገፀ ምድርን የውሃ ሀብት በማሻሻል የግብርና ልማቱን ከዝናብ ጥገኝነት ለማላቀቅ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ነው የተናገሩት። ‎‎በክልሉ በዘንድሮዉ የተፋሰስ ልማት ስራ በሁሉም ወረዳዎች በ101 ተፋሰሶች፤ 64 ሺህ ሄክታር የተራቆተ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ከቢሮው የተገኘ መረጃ ያመለክታል ።
የአባያና ጫሞ ሀይቆችን ከስጋት መታደግ የሚያስችል የተቀናጀና በጥናት የተደገፈ ስራ ይሰራል
Mar 7, 2026 179
አርባ ምንጭ፤ የካቲት 28/2018 (ኢዜአ)፦ የስምጥ ሸለቆ ተፋሰስ የሆኑ የአባያና ጫሞ ሀይቆችን ከስጋት ለመታደግ የተቀናጀና በጥናት የተደገፈ ስራ እንደሚሰራ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ አስተባባሪነት የአባያና ጫሞ ሀይቆች የሚያስከትሉትን ተጽእኖ መቀነስ የሚያስችል የባለድርሻ አካላት ውይይት በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ነው። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ በዚህ ጊዜ እንደገለጹት የአባያና ጫሞ ሀይቆችን በአግባቡ መጠቀም ባለመቻሉ ከፀጋነት ወደ ስጋትነት እየተቀየሩ መሆናቸውን ገልጸዋል።   በተለይ በጋሞ፣ በጋርዱላ፣ በኮንሶና በቡርጂ ዞኖች የሚገኙ አርሶ አደሮችን ማሳ እንዲሁም በተለያዩ መሠረተ ልማቶች ላይ አደጋ እያስከተሉ ይገኛሉ ብለዋል። በመሆኑም ሐይቆቹን ከስጋት ለመታደግ የተቀናጀና በጥናት የተደገፈ ስራ እንደሚጠናከር ገልጸዋል፡፡ ተፋሰሶቹ የተፈጥሮ ስነ-ምህዳር፣ የፍራፍሬ፣ የብዝሃ ህይወት የቱሪዝምና የቀጣናዊ ልማት ማሳለጫዎች መሆናቸውን ጠቅሰው ከስጋት ወደ ሀብት ምንጭነት ለመቀየር የባለድርሻ አካላት ሚና ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። በውሃው ዘርፍ የረጅም ጊዜ ልምድ ያለው አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የዘርፉን ችግሮች ለመቅረፍ እያደረገ ያለውን ጥረት አድንቀው የክልሉ መንግስት የበኩሉን እንደሚወጣም አረጋግጠዋል።   የማዕድን ሚኒስትርና የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሰብሳቢ ኢንጂነር ሀብታሙ ተገኝ በበኩላቸው የአባያና ጫሞ ሃይቆችን በዘላቂነት መጠቀም ለሃገር ሁለንተናዊ ብልጽግና ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡ በአርባ ምንጭና አካባቢው መልከ ብዙ ፀጋዎች መኖራቸውን ጠቅሰው የሀይቆቹን ትሩፋት ለማጉላት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ በአግባቡ ሊከናወን እንደሚገባ ጠቁመዋል። በተገኙ ጥናቶች መሠረት የተፋሰሶቹን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት የተለያዩ ፕሮግራሞች፣ ስትራቴጂዎችና ፕሮጀክቶች ተቀርጸው መተግበር እንዳለባቸውም አመልክተዋል።   የአባያና ጫሞ ሀይቆች የውሃ መጠን መጨመር፣ የተፋሰሱ ወንዞች ሙላትና ደለል ከፍተኛ አካባቢያዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጽዕኖዎችን እያስከተሉ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት አብደላ ከማል(ዶ/ር) ናቸው። የአባያና ጫሞ እንዲሁም ሌሎች ተፋሰሶች በተቀናጀ ሁኔታ ካልተመሩ ተጽዕኖው ከሀይቆቹ ዳርቻ አልፎ ሰፊ ቦታዎችን ሊያዳርስ እንደሚችል በጥናት መረጋገጡንም ጠቅሰዋል። ዩኒቨርሲቲው በተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ምክንያቶች የሚከሰቱ ተግዳሮቶችን በሳይንሳዊ መንገድ ለመከላከል የጀመረውን ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ተናግረዋል። በመድረኩ የፌዴራልና የክልል ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የስራ ኃላፊዎችና ተመራማሪዎች፣ ባለሀብቶች፣ የጋሞ ሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶችና ሌሎችም እየተሳተፉ ነው።
የኢትዮጵያ የአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ተምሳሌታዊ ተግባር ነው
Mar 7, 2026 159
አዲስ አበባ፤ የካቲት 28/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራን ጨምሮ በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና (Climate-smart agriculture) አርአያ የሚሆን ስራ እያከናወነች እንደምትገኝ የዓለም ባንክ ከፍተኛ የግብርና ባለሙያ ቲም ሮበርትሰን ገለጹ። ለአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና (Climate-smart agriculture) ሁሉን አቀፍ እይታ ያለው የግብርና ምርታማነት አማራጭ መሆኑን የዘርፉ ባለሙያዎች ይገልጻሉ። የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት ይጠበቅባቸዋል ይህ የአሰራር ዘዴ የግብርና ምርታማነት ብቻ ሳይሆን ለአደጋዎች የማይበገር አቅም መገንባትና ለአየር ንብረት ተስማሚ መሆን እንዳለበት ያስቀምጣል። ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነች ትገኛለች። ድርቅን የሚቋቋሙ ሰብሎችን ማምረት፣ አረንጓዴ አሻራ፣ የስንዴ ምርታማነት፣ የኢትዮጵያ የማዳበሪያ እና የጤናማ አፈር ፍኖተ ካርታ፣ አነስተኛ ይዞታ ያላቸውን የመስኖ ስራዎች ማስፋትና የተራቆቱ መሬቶችን በአካባቢ ጥበቃ ስራ ወደ ነባር ይዞታቸው መመለስ ከተከናወኑ ተግባር መካከል ይጠቀሳሉ። የዓለም ባንክ ከፍተኛ የግብርና ባለሙያ ቲም ሮበርትሰን ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና እየገነባች ያለችው አቅም የሚደነቅ መሆኑን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ስኬታማ ስራዎችን እያከናወነች እንደሚገኝ ጠቅሰው እንደ አረንጓዴ አሻራ ባሉ ኢኒሼቲቮች የቀጣናው ሀገራት ተጠቃሚ ሊሆኑ እንደሚገባ ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የዘርፉ ስኬቶች ለማስፋት መንግስት፣ ቀጣናዊ ተቋማት እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ይበልጥ ተቀራርበው መስራት እንዳለባቸውም አመልክተዋል። ኢትዮጵያን ጨምሮ በቀጣናው የሚገኙ ሀገራት በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ያላቸውን አቅም የበለጠ ማጠናከር እንደሚኖርባቸውም ነው ባለሙያው የገለጹት። በዚህ ረገድ የዓለም ባንክ ከመንግስታት ጋር የግሉ ዘርፍ በአየር ንብረት ተስማሚ ግብርና ያለውን የኢንቨስትመንት ተሳትፎ ለማሳደግና በተለይም ለወጣቶች የስራ ዕድል ለመፍጠር እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ኢኖቬሽን፣ ዲጂታል መፍትሄዎች፣ ዘላቂ የኢነርጂ አጠቃቀም እና ለአየር ንብረት ተስማሚ ግብርናን ማሳደግ ወሳኝ መሆኑንም ነው ያነሱት። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ የዓለም የግብርና ፋይናንስ ከፍተኛ ለውጥ ማሳየቱን ገልጸው ሀገራት ፋይናንስ በዘላቂነት የሚያመጡ አጋርነቶችን መፍጠር እንዳለባቸው መክረዋል። ለዚህ ተቋማት ትስስራቸውን ማጠናከር፣ አማራጭ ፋይናንስ መፈለግ፣ እሴት መጨመር ትኩረት መስጠት እና ለጋራ ግብ በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል።
በጋምቤላ ክልል ወይና ደጋማ አካባቢዎች የሚኖረው የዝናብ ስርጭት ለበልግ እርሻ አመቺ  ነው
Mar 6, 2026 281
ጋምቤላ ፤ የካቲት 27/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል ወይና ደጋማ አካባቢዎች በቀጣዮቹ ሶስት ወራት የሚኖረው የዝናብ ስርጭት ለበልግ እርሻ አመቺ መሆኑን በኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት የጋምቤላ ክልል ሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል አስታወቀ። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ሀገራት ለዓለም አቀፍ ቃል ኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል በኢንስቲትዩቱ የጋምቤላ ክልል የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎት ማዕከል መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ ተስፋሁን ዓለሙ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በክልሉ ወይና ደጋማ አካባቢ በቀጣይ ወራት የሚኖረው የበልግ ዝናብ ለእርሻ ስራ ተስማሚ ነው። በክልሉ ወይና ደጋማ የአየር ፀባይ ያለው የማጃንግ ዞን በቀጣዩቹ ሶስት ወራት የሚኖረው የዝናብ ስርጭት ለእርሻ ስራና ለእንስሳት ግጦሽ አመቺ ሁኔታን እንደሚፈጥር የአየር ትንበያ መረጃ ያመለክታል ብለዋል። በተለይም በዞኑ ቀድመው ለሚዘሩ የሰብል ዓይነቶችና ለመኸር እርሻ ስራ ዝግጅት በቂ የዝናብ ስርጭት እንደሚኖር መተንበዩን አመላክተዋል ። በሌላ በኩል ደግሞ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት በክልሉ ቆላማ አካባቢዎች ጠንከር ያለ የሙቀት መጠን እንደሚኖር የትንበያ መረጃዎች እንደሚያሳዩ ገልጸዋል። በመሆኑም የከርሰ ምድርና የገጸ ምድር የውሃ መጠን መቀነስ ሊኖር ስለሚችል ህብረተሰቡ ውሃን በአግባቡ መጠቀም እንዳለበት ምክር ሃሳብ ሰጥተዋል። እንዲሁም ከሙቀቱ መጨመር ጋር ተያይዞ በሰዎች ላይ የቆዳ ሽፍታ ሊከሰት ስለሚችል ማህበረሰቡ ጥንቃቄ ሊያደርግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ሀገራት ለዓለም አቀፍ ቃል ኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል 
Mar 5, 2026 198
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2018 (ኢዜአ)፡-የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አስከፊ ተፅዕኖ ለመቀነስ ሀገራት ለዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃል ኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ የ‎ዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ገለጸ። የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት ይጠበቅባቸዋል ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ተፈፃሚነት ያላት ቁርጠኝነት ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገብ እንዳስቻላት በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአየር ንብረት ተቋማዊ ልማት አማካሪ መንሱር ደሴ ገልጸዋል። ከየካቲት 23/2018 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ አራት ቀናት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው የ‎ዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ‎የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና የአውደ ጥናት የምክክር መድረክ ተጠናቋል። በአውደ ጥናቱ ማጠናቀቂያ ላይ ‎የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ፤ የአካባቢና የሥነ-ምኅዳር ደኅነንት ለማስጠበቅ ትብብርን ማጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል።   አውደ ጥናቱም የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመቀነስ ተግባራዊ የተደረጉ መርሃ ግብሮችና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ስኬታማ የልምድ ልውውጥና ግብዓት እንደተገኘበት ገልጸዋል። በፖሊሲዎችና የትኩረት መስኮች የተደረገው ውይይትም የዕውቀት ሽግግር የተደረገበት መሆኑን ተናግረዋል። ‎ዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የመንግሥታቱን ድርጅት የአየር ንብረት ስምምነት መነሻ በማድረግ ለተለያዩ ሀገራት የገንዘብ ድጋፍ እያቀረበ እንደሚገኝ አንስተዋል። ሀገራትም የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለውን አስከፊ ተፅዕኖ ለመቀነስ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ተፈፃሚነት በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ የማይበገር አረንጓዴ ኢኮኖሚ ለመገንባት የሚያደርጉትን ጥረት እንደሚያግዝ አረጋግጠዋል።   በፕላንና ልማት ሚኒስቴር የአየር ንብረት ተቋማዊ ልማት አማካሪ መንሱር ደሴ በበኩላቸው፤ በአውደ ጥናቱ ከ14 የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ 150 ሙያተኞች መሳተፋቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ ቅነሳ ዓለም አቀፍ ስምምነትና ቃልኪዳኖች ትግበራ ያላት ቁርጠኝነት በልማት አቅጣጫዎቿ ላይ ተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ መሆኑን አስረድተዋል። በአውደ ጥናቱም ኢትዮጵያ በ‎ዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በተደረገ ድጋፍ የተከናወኑ የልማት ሥራዎች በተሞክሮነት መቅረባቸውን ተናግረዋል። ከሀምሌ ወር ጀምሮ ለአራት ዓመታት የሚተገበረው ‎የዓለም አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም መርሃ ግብርም ከኢትዮጵያ የልማት አቅጣጫዎች ጋር ተጣጥመው እንደሚተገበሩ አንስተዋል።
በምስራቅ ሸዋ ዞን የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት ያደረጉ ችግኞች እየተዘጋጁ ነው
Mar 4, 2026 271
አዳማ ፤ የካቲት 25/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ምስራቅ ሸዋ ዞን የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት ያደረጉና ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማፍላት ስራ እየተሰራ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽህፈት ቤት አስታወቀ። በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ ነው በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት ሃገራዊ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ሐምሌ 2011 ዓ.ም መጀመሩ ይታወቃል። በምስራቅ ሸዋ ዞን ግብርና የጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አብነት ዘገየ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በዞኑ 11 ወረዳዎች ባሉ የችግኝ ማፊያ ጣቢያዎች ለመጪው ክረምት የሚተከሉ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ ተጀምሯል።   ችግኝ ጣቢያዎቹ ለአረንጓዴ አሻራ ዘመቻው የተለያየ ዝርያ ያላቸው ችግኞችን አፍልቶ በማቅረብ ረገድ እያበረከቱ ያለው አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን አስታውሰዋል። ዘንድሮም ለማዘጋጀት ከታቀደው ከ284 ሚሊዮን በላይ ችግኞች ውስጥም 241 ነጥብ 4 ሚሊዮን ችግኞችን የማፍላት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። ቀሪ ችግኞችን የማፍላት ሥራም እስከ መጪው ግንቦት ወር ድረስ ለማጠናቀቅ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። በችግኝ ዝግጅቱም በአብዛኛው የአየር ንብረት መዛባትን ለመከላከል ለሚያገለግሉ የደን እና ጥምር ደን ዝርያዎች ትኩረት የተሰጠ መሆኑን አስረድተዋል። በተጨማሪም ለአርሶ አደሩ ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታን የሚያስገኙና እና ለምግብነት የሚውሉ 26 ነጥብ 7 ሚሊዮን የፍራፍሬ ችግኞችን ያካተተ የዘር ዝግጅት መደረጉንም ተናግረዋል። የዘንድሮ ዓመት የችግኝ ተከላ የአካባቢውን ሥነ ምሕዳር መሠረት በማድረግ የሚከናወን መሆኑን ጠቁመው በዞኑ ባለፉት ዓመታት ከተተከሉ ችግኞች ከ85 በመቶ በላይ መጽደቃቸውን አስታውቀዋል። በአሁኑ ወቅትም የተተከሉ ችግኞችን ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ የመጠበቅና የመንከባከብ ሥራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ነው ያረጋገጡት። በዘንድሮው ዓመት በዘርፉ የተቀመጠውን እቅድ ለማሳካትም የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ተቆፍረው መዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል።
የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት ይጠበቅባቸዋል 
Mar 3, 2026 241
አዲስ አበባ፤ የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፦የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት መገንባት እንደሚጠበቅባቸው የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) ገለጸ። "በምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ የሚቋቋም ግብርናን ማስፋፋት" በሚል መሪ ሃሳብ ለሁለት ቀናት የሚቆይ ቀጣናዊ የምክክር መድረክ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።   በኢጋድ፣ የዓለም ባንክ የአፍሪካ ቢሮ፣ የሥርዓተ ምግብ ፕሮግራም ለምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ፣ የደቡባዊ አፍሪካ የግብርና ምርምርና ልማት ማስተባበሪያ ትብብር በተዘጋጀው መድረክም የግብርና ማሻሻያ ምክረ ሀሳቦችን እንደሚያፈልቅ ይጠበቃል። የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) ተወካይ ዳህር ኤልሚ፤ በአየር ንብረትና በሥነ-ምኅዳር ደኅንነት የሚከሰት ለውጥ የግብርና ምርታማነት ላይ ጫና እያሳደረ ነው ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ የሚያስከትለው የአፈር መራቆት፣ ድርቅ፣ ጎርፍ፣ ዝናብ እጥረትና በርሃማነት የምስራቅ አፍሪካ የግብርና ምርታማነትና የምግብ ፍጆታ ላይ አሉታዊ ጫና እንደሚያሳድሩ ገልጸዋል። በዚህም የቀጣናው ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አስተማማኝ የግብርና ሥርዓት ለመገንባት የቴክኖሎጂ፣ የግብዓትና የመረጃ ትንተና አቅም መገንባት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣንም የቀጣናውን ሀገራት የግብርና ምርታማነት የሚያሻሽል የአየር ሁኔታ የመረጃ ትንተና ተደራሽ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል።   በኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት የተፈጥሮ ሃብትና የአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ፕሮግራም ዳይሬክተር አወቀ ሙሉዓለም በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ሥርዓት ውጤት እያስመዘገበ ነው ብለዋል። የአረንጓዴ አሻራ፣ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎችም የተራቆቱ አካባቢዎች እንዲያገግሙ በማድረግ የአርሶና አርብቶ አደሩን የግብርና ምርታማነት እያሳደገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዓለም ባንክ ከፍተኛ የግብርና ባለሙያ ቲም ሮበርትሰን፤ የግብርና ምርታማነት የሚያዘምኑ የፋይናንስና የቴክኖሎጂ ውጤቶችን በማስፋት የቀጣናው ሀገራት አርሶ አደሮችን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል።   በኢትዮጵያ የኒውዝላንድ አምባሳደር የኢጋድና የአፍሪካ ሕብረት ቋሚ ተወካይ አምባሳደር ኦሊቪያ ኦዌን በበኩላቸው፤ የግብርና ምርታማነትን ማረጋገጥ ለአፍሪካ ዕድገትና ብልጽግና ወሳኝ ነው ብለዋል።   የቀጣናውንና አፍሪካን የግብርና ሥርዓት ለማዘመን በሚደረገው ጥረትም የኒውዝላንድ መንግስትና የልማት አጋሮች የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በፎረሙ ላይ የኢጋድ አባል ሀገራት ተወካዮች፣ ፖለሲ አውጪዎች፣ የልማት አጋሮች፣ የግሉ ዘርፍ ተወካዮችና ተመራማሪዎች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።
በሚቀጥሉት አስር ቀናት የበልግ ዝናብ ስርጭትና መጠን ይጠናከራል
Mar 3, 2026 187
አዲስ አበባ፤ የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፦በቀጣዮቹ አስር ቀናት በሀገሪቱ የበልግ ሰብል አብቃይ አካባቢዎች የዝናብ መጠንና ስርጭት በከፍተኛ ሁኔታ እየተስፋፋና እየተጠናከረ እንደሚሄድ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ። ኢንስቲትዩቱ አራተኛውን የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስራ ሊያስጀምር ነው በኢንስቲትዩቱ የሚቲዎሮሎጂ ትንበያ፣ምክር አገልግሎት እና ምርምር ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አሳምነው ተሾመ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ለዝናብ መፈጠር ምቹ የሆኑ የሚቲዎሮሎጂ ገጽታዎች ይበልጥ እየተጠናከሩ መሆናቸውን የትንበያ መረጃዎች ያመላክታሉ። የዝናብ ስርጭቱ የሚሸፍናቸው ደቡብና ደቡብ ምስራቅ ኢትዮጵያ (ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው የሆኑ አካባቢዎች)፣ የስምጥ ሸለቆና አጎራባች አካባቢዎች፣ የመካከለኛውና የደቡብ ምዕራብ የሀገሪቱ ክፍሎች ምስራቅና ሰሜን ምስራቅ አካባቢዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። በእነዚህ አካባቢዎች ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ የሚጠበቅ ሲሆን፣ በአብዛኛው ስፍራዎች የዝናብ መጠኑ መደበኛና ከመደበኛ በላይ እንደሚሆን ገልጸው፤አልፎ አልፎም ከባድ ዝናብ ሊኖር እንደሚችል ተናግረዋል። የዝናቡ መሻሻል በተለይም ለበልግ አብቃይ አርሶ አደሮች ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል። በበልግ እየጣለ ያለው ዝናብ የማሳ ዝግጅትና ዘር፡ የአፈር እርጥበትን በማሻሻል አርሶ አደሩ የተለያዩ ሰብሎችን መዝራት እንዲችል ምቹ ሁኔታን በመፍጠር አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል ብለዋል። ለቋሚ ተክሎች፡ ቀደም ብለው ለተዘሩ የበልግ ሰብሎችና በአካባቢው ለሚገኙ ቋሚ ተክሎች ዕድገት ያለውን አስተዋጽኦም ገልጸዋል። ለውሃ አጠር አካባቢዎችም አርሶ አደሩና አርብቶ አደሩ የሚጥለውን የዝናብ ውሃ በማሰባሰብና በማከማቸት ለቀጣይ እንዲጠቀም ምክረ ሀሳብ አቅርበዋል። በበልግ የሚጥለው ዝናብ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የገጸ ምድር ውሃ መጠን በተለያዩ ተፋሰሶች ላይ እንደሚጨምርም ገልጸዋል። በዚህም ኦሞ ጊቤ፣ ስምጥ ሸለቆ፣ የላይኛውና መካከለኛው አዋሽ፣መካከለኛና ታችኛው አባይ፣ ገናሌ ዳዋ እና ዋቤ ሸበሌ ተፋሰሶች የተሻለ እርጥበት እንደሚያገኙ ይጠበቃል ብለዋል። በዚህም የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የውሃ ማጠራቀሚያዎችን በመጠቀም የውሃ መጠናቸው ከፍ እንዲል ያደርጋል ብለዋል። ከዚሁ ጋር በተያያዘ በአንዳንድ የአገሪቱ ክፍሎች አሁንም ከፍተኛ የቀን ሙቀት እንደሚቀጥል ገልጸዋል። በዚህም በጋምቤላ፣ አፋር፣ ሶማሌ፣ ቤንሻንጉል ጉሙዝና ምዕራብ አማራ አካባቢዎች የቀኑ ከፍተኛ ሙቀት ከ33 እስከ 37 ነጥብ 2 ዲግሪ ሴልሺየስ ሊደርስ እንደሚችል የትንበያ መረጃዎች ያሳያሉ ተብሏል።
ኢንስቲትዩቱ አራተኛውን የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስራ ሊያስጀምር ነው
Mar 3, 2026 152
ዳንቦያ፤ የካቲት 24/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣ ከንባታ ዞን አራተኛውን ዘመናዊ የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳር የመትከል ተግባርን በማጠናቀቅ ስራ ለማስጀመር የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ እንደሚገኝ አስታወቀ። የኢንስቲትዩቱ ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ እንደገለጹት፤ ኢንስቲትዩቱ በክልሉ ከንባታ ዞን ዳንቦያ ወረዳ ዳቶ ዳርሀቦራ ተራራ ላይ ነው ዘመናዊ የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳሩን የተከለው። ራዳሩ በ250 ኪሎ ሜትር ራዲየስ ውስጥ ያለን የአየር ሁኔታ መረጃ የመሰብሰብ አቅም ያለው ሲሆን፣ የትንተናና የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥራዎችን በተሻለ ጥራት ለመከወን ያስችላል ብለዋል። በ14 ሜትር ከፍታ ላይ የተተከለው ይህ ራዳር የዝናብ መጠንን፣ የንፋስ ፍጥነትን፣ የዳመና እንቅስቃሴንና ዝናብ ያዘለ አውሎ ነፋስን የመሳሰሉ መረጃዎችን ከርቀት በመቃኘት ለዋናው የዳታ ማዕከል መረጃ ያስተላልፋል ብለዋል። ይህ የራዳር ጣቢያ በኢትዮጵያና በፊንላንድ መንግሥታት ድጋፍ 13 ሚሊዮን ዩሮ በሚጠጋ በጀት ወደ ሥራ ከሚገቡ ፕሮጀክቶች አንዱ መሆኑን የገለፁት ዳይሬክተሩ፤ አገልግሎቱን በቴክኖሎጂ ለማዘመንና የተሳለጠ መረጃ ለማቅረብ ትልቅ ፋይዳ እንዳለውም አብራርተዋል። በፕሮጀክቱ የተጠቀሰውን ጨምሮ አራት የአየር ሁኔታ መከታተያ ራዳሮች፣ 10 የአየር ብክለት መከታተያ ጣቢያዎች፣ 10 የመብረቅ መከታተያና ሌሎች የተቀናጁ የሚቲዎሮሎጂ መሠረተ ልማትን የመገንባት ሥራን ያካተተ ነው ብለዋል። ኢንስቲትዩቱ በሀገር አቀፍ ደረጃ በ12 ስልታዊ ቦታዎች ላይ የራዳር ጣቢያዎችን ለመትከል እቅድ መያዙን ጠቁመው፤ አራተኛውን ጣቢያ በማጠናቀቅ የሚቲዎሮሎጂ አገልግሎቱን የማሳደግ አቅሙን አንደሚያጠናከር አስረድተዋል። ራዳሩ በተተከለበት አካባቢ የኃይል መቆራረጥም ሆነ የመረጃ ልውውጥ እንዳይቋረጥ የፀሐይ ብርሃን ኃይል (ሶላር ኢነርጂ) እየተገጠመ ይገኛል ብለዋል።   የፕሮጀክቱን የመጨረሻ ምዕራፍ ለመጎብኘት በስፍራው የተገኙት በፊንላንድ ኤምባሲ የትብብር ዘርፍ ኃላፊ ቶሚ ሳርኪኦጃ መንግሥታቸው የኢትዮጵያን ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት በመደገፉ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል።  
በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ ነው
Mar 3, 2026 128
ነጌሌቦረና፤የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል በምስራቅ ቦረና ዞን የእንስሳት መኖ እጥረት እንዳያጋጥም የመኖ ልማት ስራ ከተፋሰስ ጥበቃ ጋር ተቀናጅቶ እየተከናወነ መሆኑን የዞኑ ግብርና ጽሕፈት ቤት ገለጸ። የጽሕፈት ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ ኩልሌ ሸና እንደገለጹት፤ ዞኑ ቆላማና ዝናብ አጠር በመሆኑ በየጊዜው የሚያጋጥመውን የእንስሳት መኖ እጥረት በዘላቂነት ለመቋቋም ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። ለዚህም በዘንድሮው የበጋ ወቅት ሕብረተሰቡን በማሳተፍ 105 ተፋሰሶችን መሠረት ያደረገ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ ይገኛል። በዞኑ በሁሉም ወረዳዎች በሚገኙ ተፋሰሶች ላይ የሚካሄደው የተቀናጀ የልማት ሥራ ከ52 ሺህ 500 ሄክታር በላይ መሬት የሚያካልል መሆኑን አቶ ኩልሌ ጠቁመዋል። ከዚህ ውስጥ በሰው ሰራሽ ጫና እና ከልክ ያለፈ ግጦሽ የተራቆተ ከ38 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ተከልሎ መልሶ እንዲያገግም እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። እስካሁን በተከናወነው እንቅስቃሴ 24 ሺህ 430 ሄክታር የግጦሽ መሬት ከሰውና ከእንስሳት ንክኪ ተከልሎ እንዲያገግም የተደረገ ሲሆን፣ ይህም መኖን በዘላቂነት ለማግኘት የሚደረገውን ጥረት ያግዛል። ከተፈጥሮ ግጦሽ በተጨማሪም በክረምትና በበጋ መስኖ የታገዘ የመኖ ልማት ለማስፋፋት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ምክትል ኃላፊው አስታውቀዋል። በዘንድሮው የተፋሰስ ልማት ከተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት መካከል የአፈርና የድንጋይ እርከን እንዲሁም የጎርፍ መፋሰሻ ቦይ ግንባታ እየተከናወነ ሲሆን የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች ዝግጅትንም ጠቅሰዋል። በነዚህ የልማት ሥራዎች ላይ አርሶና አርብቶ አደሮች፣ የወጣቶችና የሴቶች አደረጃጀቶች በንቃት ተሳትፈዋል። ከዚህም ባለፈ በበልግና በክረምት የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን የማዘጋጀት ሥራ እየተከናወነ መሆኑ ተገልጿል። የሊበን ወረዳ የጎቢቻ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ወርቁ አለባቸው በሰጡት አስተያየት፤ አካባቢያቸው ዝናብ አጠር በመሆኑ በተደጋጋሚ ለሚከሰተው የእንስሳት መኖ እጥረት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ባለፉት ዓመታት ከደረሰባቸው ጉዳት በመማር አሁን ላይ በአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ላይ በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛው የቀበሌው ነዋሪ አቶ አልዬ ኢብራሂም በበኩላቸው፤ የአረንጓዴ አሻራ እና የእንስሳት መኖ ልማት ለአርብቶ አደሩ ማህበረሰብ የህልውና ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰው፤ ድርቅንና የአካባቢ መራቆትን ለመቋቋም በአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ላይ ቅድሚያ በመስጠት እንደሚሳተፉ አረጋግጠዋል።    
የኢትዮጵያ የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ ናቸው
Mar 2, 2026 154
አዲስ አበባ፤ የካቲት 23/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ። የ‎ዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ‎የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና አውደ ጥናት በአዲስ አበባ ተካሂዷል።   የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ‎በዚሁ ወቅት እንዳሉት የ‎ዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም በዓለም ደረጃ የአካባቢ መራቆትን፣ የብዝሃ ህይወት መመናመንን እንዲሁም በትልልቅ የውሀ አካላት ላይ እየደረሱ ያሉ ጉዳቶችን ለመከላከል ድጋፍ የሚያደርግ ዓለም አቀፍ ተቋም ነው። ተቋሙ ለሚቀጥሉት አራት ዓመታት የሚሆን ፕሮግራም ተግባራዊ እንደሚያደርግ ገልጸው የአውደ ጥናቱ ዓላማ ከዚህ ቀደም የተተገበሩ ፕሮግራሞችን ለመገምገም መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ በብዝሃ ህይወት ጥበቃ እና የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል ረገድ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ተግባራዊ መደረጋቸውን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ልማት መርሃ ግብሮች በዓለም አቀፍ ደረጃ በምሳሌነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ በእነዚህ ስራዎች አማካይነት እውቅና እያገኘችበት እንደምትገኝም ገልጸዋል።   የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ በበኩላቸው የምስራቅ አፍሪካ ሰፊ የተፈጥሮ ሀብት እና እምቅ አቅም እንዳለው ጠቅሰው፥ ‎ይሁን እንጂ እንደ ብዝሃ-ህይወት መጥፋት፣ የመሬት መራቆት እና ብክለት ያሉ ፈተናዎች የተደቀኑበት ቀጣና ነው ብለዋል። በመሆኑም ‎‎ቀጣናዊና፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት በአየር ንብረት ለውጥ የሚደርሱ ጫናዎችን ለመቋቋም በትብብር መሥራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል። የ‎ዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል በተለያዩ መንገዶች የገንዘብ ድጋፍ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ከዘላቂ ልማትና ከአረንጓዴ የኢኮኖሚ እድገት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ እርምጃዎችን እየወሰደች ነው 
Mar 2, 2026 184
አዲስ አበባ፤ የካቲት 23/2018(ኢዜአ)፦‎ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ከዘላቂ ልማትና ከአረንጓዴ ኢኮኖሚ እድገት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ እርምጃዎችን እየወሰደች መሆኑን የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ገለጹ። ‎ ‎የ‎ዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም ‎የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና አውደ ጥናት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማትና በታዳሽ ኃይል ለዓለም የስኬት አርዓያ ሆናለች -የሮማኒያ አምባሳደር የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ስዩም መኮንን ‎በዚሁ ወቅት፥ ‎የአየር ንብረት ለውጥ፣ የሥነ-ሕይወት መጥፋት እና ብክለት ‎በምድራችን የአካባቢ ደህንነት፣ የምግብ ዋስትና እና የልማት ጉዞ ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይ ‎በምስራቅ አፍሪካ የሚከሰቱ ድርቅና የአካባቢ መራቆት በማህበረሰቡና በስርዓተ ምህዳሩ ላይ አስከፊ ጉዳት እያስከተሉ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ‎አካባቢን መጠበቅና የአየር ንብረት ለውጥን መቋቋም የህልውና ጉዳይና የብልጽግና መሰረት መሆኑን ጠቁመዋል። ‎ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖን ለመከላከል ለአፍሪካና ለዓለም ምሳሌ የሚሆን አኩሪ የአረንጓዴ ልማት ተግባራትን እያከናወነች እንደምትገኝ ተናግረዋል። ከዘላቂ ልማትና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ ከመገንባት ጋር የተጣጣሙ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎቿ ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ‎በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በሰባት ዓመታት ውስጥ ብቻ ከ48 ቢሊዮን በላይ ችግኞችን በመትከል ታላቅ የደን ልማት ለዓለም ማሳየቷንም አንስተዋል። ‎እንደ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ያሉ የታዳሽ ሃይል ልማት ፕሮጀክቶች፣ የከተሞች የኮሪደር ልማት፣ የወንዝ ዳርቻ ልማት፣ የሌማት ትሩፋት፣ የበጋ መስኖ ስንዴ እና ሌሎችም የልማት ኢኒሼቲቮች ከራሷ አልፎ ለቀጣናው ዘላቂ ዕድገት ያላትን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጡ ናቸው ብለዋል። ‎የአውደ ጥናት የምክክር መድረኩ በአየር ንብረት ለውጥ ምላሽ ዙሪያ የትብብር ሥራዎችን በማስፋት የጋራ ዕድገትን ለማረጋገጥ የሚበጁ ምክር ሀሳቦችን ለማመንጨት እንደሚረዳ አንስተዋል። የዓለም አቀፉ የአካባቢ ጥበቃ ተቋም የአፍሪካ አስተባባሪ ጆንኪ ቴኑ በበኩላቸው፤ ምስራቅ አፍሪካ ሰፊ የተፈጥሮ ሀብት እና እምቅ አቅም እንዳለው ጠቅሰው፥ ‎ይሁን እንጂ እንደ ብዝሃ-ህይወት መጥፋት፣ የመሬት መራቆት እና ብክለት ያሉ ፈተናዎች የተደቀኑበት ቀጣና ነው ብለዋል። በመሆኑም ‎‎ቀጣናዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ተቋማት በአየር ንብረት ለውጥ የሚደርሱ ጫናዎችን ለመቋቋም በትብብር መሥራት እንዳለባቸው ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም