ቀጥታ፡
ዓለም አቀፍ ዜናዎች
የአፍሪካ መሪዎች ብዝሃ ህይወትን ከብሄራዊ ፖሊሲዎቻቸው ጋር ማስተሳሰር ይገባቸዋል -አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ
Nov 6, 2025 419
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 27/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ መሪዎች የብዝሃ ህይወት አጀንዳን ከብሄራዊ ፖሊሲዎቻቸው ጋር በማቆራኘት ሊተገብሩ እንደሚገባ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ ገለጹ። ከጥቅምት 23 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በቦትስዋና ጋቦሮኒ ሲካሄድ የቆየው የመጀመሪያው የአፍሪካ የብዝሃ ህይወት ጉባኤ በመሪዎች ደረጃ በተደረገ ስብስባ ተጠናቋል። በጉባኤው ላይ የሀገራት መሪዎች፣ የአካባቢ ጥበቃ ሚኒስትሮች፣ የዓለም የብዝሃ ህይወት ጥበቃ መሪዎች እና ተመራማሪዎች፣ ሀገር በቀል የማህበረሰብ መሪዎች፣ ባለሀብቶች፣ የግሉ ዘርፍ ተዋንያን፣ የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት፣ ዓለም አቀፍ አጋሮች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል። “የብዝሃ ህይወትን በዘላቂነት በመጠቀም የአፍሪካን ብልጽግና ማረጋገጥ” የጉባኤው መሪ ሀሳብ ነው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ ጉባኤው አፍሪካ የተፈጥሮ ሀብቷን ለመጠበቅ በጀመረችው ጉዞ ውስጥ ታሪካዊ ሁነት መሆኑን ገልጸዋል። ከኮንጎ ጥብቅ ደን እስከ ደቡብ አፍሪካው የኬፕ የአበባ ሀብት ቀጣና በአህጉሪቷ የሚገኙ ተፈጥሯዊ ምህዳሮች የህይወት፣ ባህል እና የኢኮኖሚ እድገት ምንጮች መሆናቸውን አመልክተዋል።   የአየር ንብረት ለውጥ፣ ብክለት እና ዘላቂ ያልሆነ የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም በአፍሪካ የብዝሃ ህይወት ላይ ስጋቶችን እንደደቀኑ ተናግረዋል። የብዝሃ ህይወት ጥበቃ ላይ የተቀናጀ የተግባር ምላሽ ያስፈልጋል ያሉት አምባሳደሯ ለዘርፉ የሚያስፈልገውን መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ ይገባል ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ከአባል ሀገራት፣ ከቀጣናዊ ተቋማት፣ ሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት እና የግሉ ዘርፍ ጋር በመሆን የአፍሪካ ብዝሃ ህይወት ስትራቴጂ ከአጀንዳ 2063 እና ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የዘላቂ ልማት ግቦች ጋር በተጣጠመ መልኩ እንዲተገበር በትብብር እንደሚሰራ ነው የገለጹት። ብዝሃ ህይወት እንደ ተጓዳኝ ጉዳይ ሳይሆን ለአፍሪካ ሰላም፣ አይበገሬነት እና ዘላቂ ልማት ባለው ቁልፍ ድርሻ ሊታይ እንደሚገባ ጠቅሰው በዚህ ረገድም የአፍሪካ መሪዎች ብዝሃ ህይወት ከብሄራዊ ፖሊሲዎች ጋር ማስተሳሰር እንዳለባቸው አሳስበዋል። ወጣቶች እና ሀገር በቀል ማህበረሰቦችን ማብቃት እንዲሁ በፋይናንስ እና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዓለም አቀፍ እኩልነት ለማስፈን መትጋት ትኩረት እንደሚያሻቸው ነው ያነሱት። የአፍሪካ ብልፅግና አረንጓዴ፣ ሁሉን አቀፍ እና ተፈጥሮን መሰረት ያደረገ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። የጋቦሮኒው ጉባኤ የአፍሪካ ብዝሃ ህይወት ድንጋጌ ቀጣይ ለሚመጡ ትውልዶች መሰረት የሚጥል እንደሚሆንም ገልጸዋል። ጉባኤው በአፍሪካ ብዝሃ ህይወት ሀብቶች፣ እድሎች፣ ፈተናዎችና ቀጣይ እርምጃዎች በዋናነት መምከሩን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
በሄይቲ እና ጃማይካ ከባድ አውሎ ነፋስ ባስከተለው ጎርፍ ሳቢያ የበርካቶች ሕይዎት አለፈ
Oct 31, 2025 559
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 21/2018 (ኢዜአ)፡-በሄይቲ እና ጃማይካ የተከሰተው ‘ሃሪኬን ሜሊሳ’ የተሰኘው ወጀብና ዝናብ የቀላቀለ ከባድ አውሎ ነፋስ ባስከተለው የጎርፍ መጥለቅለቅ ሳቢያ እስካሁን የ49 ሰዎች ሕይዎት ማለፉ ተሰምቷል። በሄይቲ የ30 ሰዎች ሕይዎት ማለፉን እና ከ20 በላይ ሰዎች የገቡበት አለመታወቁን የሀገሪቱ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል። እስካሁን ያሉበት ሁኔታ ያልታወቁ ሰዎችን የመፈለጉ ሥራም መቀጠሉን ባለሥልጣናቱ ለአልጄዚራ ገልጸዋል።   ከዚሁ ጋር በተያያዘም የሟቾች ቁጥር ሊያሻቅብ እንደሚችል አመላክተዋል። እንዲሁም የአውሎ ነፋሱ ሰለባ በሆነችው ሌላኛው ሀገር ጃማይካ የ19 ሰዎች ሕይዎት ማለፉን ሮይተርስ ዘግቧል። እስካሁን ከተመዘገቡት በጣም ኃይለኛ የአትላንቲክ አውሎ ነፋሶች አንዱ እንደሆነ የተነገረለት ሃሪኬን ሜሊሳ በሠዓት 295 ኪሎ ሜትር እንደሚከንፍ ተገልጿል። አውሎ ነፋሱ የጃማይካን ምዕራባዊ ክልል በመምታት አስከፊ ጉዳት ማድረሱን የሀገሪቱ ባለሥልጣናት ተናግረዋል።   ሃሪኬን ሜሊሳ በካሪቢያን ቀጣና ኩባ፣ሄይቲ እና ጃማይካ በሰው ሕይወት እንዲሁም በንብረት ላይ የከፋ ጉዳት ማድረሱ ተሰምቷል። ይህን ተከትሎም በካሪቢያን የሚገኙ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ከኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ውጭ መሆናቸውን ዘገባው አመላክቷል። የኤሌክትሪክ አቅርቦቱን ለመመለስና አካባቢዎቹንም የማጽዳት ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙም ተጠቅሷል።
የአፍሪካ ህብረት የ30 ቢሊዮን ዶላር የአቪዬሽን መሰረተ ልማት የኢንቨስትመንት እቅድ ይፋ አደረገ
Oct 31, 2025 465
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 21/2018 (ኢዜአ):-የአፍሪካ ህብረት የአህጉሪቷን የአቪዬሽን መሰረተ ልማት ማዘመንን አላማ ያደረገ የ30 ቢሊዮን ዶላር የኢንቨስትመንት እቅድ ዛሬ ይፋ አድርጓል። ከጥቅምት 18 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በአንጎላ ሉዋንዳ ሲካሄድ የነበረው ሶስተኛው የአፍሪካ መሰረተ ልማት ፋይናንስ ጉባኤ ዛሬ ተጠናቋል። በጉባኤው ላይ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የአንጎላ ፕሬዝዳንት እና የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀ መንበር ጆአኦ ሎሬንቾ፣ የህብረቱ ተቋማት አመራሮች፣ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች፣ የአየር መንገዶች ዋና ስራ አስፈጻሚዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። ከጉባኤው ጎን ለጎን በአፍሪካ ነጻ የአየር ትራንስፖርት ገበያ አማካኝነት የአህጉሪቷን አቪዬሽን መሰረተ ልማት በፋይናንስ በመደገፍ እና በማዘመን የተቀናጀ የአየር አገልግሎት እና ነጻ እንቅስቃሴን መፍጠር ላይ ያተኮረ ከፍተኛ የምክክር መድረክ ተከናውኗል። የአፍሪካ ህብረት የመሰረተ ልማት እና ኢነርጂ ኮሚሽነር ሌራቶ ማታቦጅ በመድረኩ ላይ በአየር ትራንስፖርት ገበያው አማካኝነት የአህጉሪቷን የአቪዬሽን መሰረተ ልማት ለማዘመን የሚውል የ30 ቢሊዮን ዶላር የኢንቨስትመንት እቅድ ዛሬ ይፋ አድርገዋል። እቅዱ አፍሪካ በቀጣይ 10 ዓመት የአቪዬሽን ዘርፉን ለማሻሻል የሚያስፈልጋትን ከ25 እስከ 30 ቢሊዮን ዶላር የፋይናንስ ክፍተት የሚሞላ እንደሆነ ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። በአፍሪካ እ.አ.አ በ2024 160 ሚሊዮን የነበረው የመንገደኞች መጠን እ.አ.አ በ2050 ወደ 500 ሚሊዮን ገደማ እንደሚደርስ የገለጸው ህብረቱ ኢንቨስትመንቱ የተሳፋሪዎችን ደህንነት ለማረጋገጥ እና አቅምን ለማጎልበት እንደሚያስችል አመልክቷል። በኢንቨስትመንት እቅዱ አማካኝነት ገንዘቡ ለአውሮፕላን ማረፊያ፣ አውሮፕላን ጣቢያ እና ጥገና ማዕከላት መሰረተ ልማት፣ የአቪዬሽን ስርዓቶች ማዘመን፣ ለሰው ኃይል ልማት፣ ለቁጥጥር ስራ፣ ለቴክኖሎጂ እና ተጓዳኝ ስራዎች እንደሚውል ተገልጿል። የአፍሪካ ህብረት 10 ቢሊዮን ዶላሩን ከአፍሪካ መንግስታት፣ ከቀጣናዊ የልማት ባንኮች እና ከባለቡዙ ወገን አጋሮች ለመሰብሰብ መታቀዱን አስታውቋል። ቀሪው 20 ቢሊዮን የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ አጋሮች፣ የሉዓላዊ ሀብት ፈንዶች (sovereign wealth funds) እና የጡረታ ፈንዶችን ጨምሮ ከግል እና የተቋማት ኢንቨስተሮች ለማግኘት መታሰቡን ነው ያመለከተው። የሀብት ማሰባሰቡ የሚከናወነው በአፍሪካ ነጻ የአየር ትራንስፖርት ገበያ ማዕቀፍ ሲሆን የ30 ቢሊዮን ዶላሩ ከእ.አ.አ 2025 እስከ 2035 ለሚተገበሩ ስራዎች የሚውል ነው። የአፍሪካ ህብረት የመሰረተ ልማት እና ኢነርጂ ኮሚሽነር ሌራቶ ማታቦጅ አቪዬሽን የትራንስፖርት አማራጭ ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ ትስስር ስትራቴጂካዊ ሞተር እንዲሁም የአጀንዳ 2063 እና የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ቁልፍ አቅም ነው ብለዋል። በኢንቨስትመንት እቅዱ የሚሰሩ ፕሮጀክቶች ዓለም አቀፍ የአረንጓዴ ልማት መመዘኛዎችን ባሟላ እና ከካርቦን ልህቀት ነጻ በሆነ መልኩ እንደሚገነቡ አመልክተዋል። ህብረቱ ዘመናዊ፣ ውጤታማ እና ዘላቂ የአቪዬሽን ኔትወርክ በመፍጠር ለአፍሪካ የኢኮኖሚ ትስስር ለማጠናከር፣ የአየር ትራንስፖርት ግንኙነት ስር እንዲሰድ እና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት እንዲያድግ በቁርጠኝነት ይሰራል ነው ያሉት።
ለአህጉሪቷ ለዘላቂና አስተማማኝ የምግብ ሥርዓት ግንባታ አባል ሀገራት ሚናቸውን መወጣት አለባቸው  
Oct 24, 2025 728
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 14/2018(ኢዜአ):-ለአህጉሪቷ አስተማማኝና ዘላቂ የምግብ ሥርዓት ግንባታ አባል ሀገራት ሚናቸውን መወጣት እንዳለባቸው በአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ ገለጹ፡፡ የአፍሪካ ኅብረት የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የውሃ እና የአካባቢ ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ ስድስተኛ መደበኛ ስብሰባውን በአዲስ አበባ አካሂዷል፡፡   በስብሰባው ላይ የአባል አገራት በግብርና፣ በእንስሳት፣ በዓሳ ሀብት፣ በገጠር ልማት፣ በውሃ፣ በአካባቢ እና በአየር ንብረት ለውጥ ዘርፎች ዙሪያ የሚሰሩ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል፡፡ በስብሰባው የሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት ፕሮግራም የማላቦ አጀንዳ (እ.ኤ.አ 2014 እስከ 2025) መጠናቀቁ የተገለጸ ሲሆን፤ በመጪዎቹ አስር ዓመታት የሚተገበረው የካምፓላ አጀንዳ (እ.ኤ.አ 2026 እስከ 2035) ጸድቋል፡፡ በአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ አካባቢ ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ እንደገለጹት፤ በአፍሪካ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ብሎም የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም አባል ሀገራት የራሳቸውን ሚና ሊወጡ ይገባል፡፡ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥም የግብርና ግብዓቶችንና ምርጥ ዘርን መጠበቀ እንዲሁም ብዝሃ ህይወትን ማልማትና መንከባከብ እንደሚገባም ተናግረዋል፡፡ ለወጣቶች የሥራ ዕድል ፈጠራና የውሃ ኃብትን ከማሳደግ አኳያም ትኩረት ሊሰጥ እንደሚገባ ጠቁመው፤ በአሁኑ ወቅት እየተመዘገቡ ያሉ ውጤቶች ተስፋ ሰጪ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ የአፍሪካ ኅብረት ልማት ኤጀንሲ - ኒፓድ የግብርና፣ የምግብ ዋስትና እና የአካባቢ ዘላቂነት ዳይሬክተር ኤስቴሪን ፎታቦንግ የካምፓላ አጀንዳ (2026–2035) በአፍሪካ የግብርና-ምግብ ሥርዓቶች ላይ የለውጥ ምዕራፍ ለመፍጠር ያለመ መሆኑ ገልጸዋል፡፡   ከአጀንዳው ግቦች መካከልም ዘላቂ የምግብ ምርትን፣ አግሮ-ኢንዱስትሪያላይዜሽንን እና ንግድን ማጠናከር፣ ለግብርና-ምግብ ሥርዓት ለውጥ ኢንቨስትመንትና ፋይናንስን ማሳደግ ብሎም የምግብ እና የተመጣጠነ ምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚሉ እና ሌሎችም ተጠቃሽ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ የአፍሪካ ኅብረት ልማት ኤጀንሲ የካምፓላ አጀንዳ ስትራቴጂ እንዲሳከ ምቹ ሁኔታዎችን ሲያዘጋጅ መቆየቱንም ጠቁመዋል፡፡ የዩጋንዳ ግብርና ሚኒስትር ዴኤታ እና የአምስተኛው የአፍሪካ ኅብረት የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የውሃ እና የአካባቢ ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ ተወካይ ፍሬድ ብዊኖ ክያኩላጋ የካምፓላ አጀንዳ የእንስሳት ሃብትን ማሳደግ ላይ ትልቅ ትኩረት ይሰጣል ብለዋል፡፡   በዚህም ለእንስሳትና ለዓሳ እርባታ ትልቅ ትኩረት እንደሚሰጥ ጠቁመው፤ የእንስሳት መኖ ማሳደግ፣ ለእንስሳት ጤና እንዲሁም የዘረመል መሻሻልም ከትኩረት መስኮች መካከል ናቸው ብለዋል፡፡ የካምፓላ አጀንዳ የአፍሪካ ግብርና ልማት መርሃ ግብር ታላላቅ ግቦች መሳካት የሚያበረክተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
የጣና ፎረም በባሕር ዳር ከተማ መካሄድ ጀመረ
Oct 24, 2025 453
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 14/2018(ኢዜአ)፦11ኛው የጣና ፎረም በባሕር ዳር ከተማ መካሄድ ጀምሯል። ከዛሬ ጥቅምት 14 እስከ 16/2018 ዓ.ም ድረስ የሚቆየው 11ኛው ጣና ፎረም በባሕር ዳር ከተማ መካሄድ ጀምሯል። በፎረሙ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር)፣ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ጨምሮ የአፍሪካ ሀገራት፣የዓለም አቀፍ፣ አህጉራዊና ቀጣናዊ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። የጣና ፎረም "አፍሪካ በተለዋዋጩ የዓለም ሥርዓት" በሚል መሪ ሃሳብ በባሕር ዳርና አዲስ አበባ ከተሞች በአፍሪካ የደህንነት ጉዳዮች ዙሪያ ለሶስት ቀናት የሚመክር ይሆናል። የአፍሪካ ሀገራት መሪዎችና ተሳታፊ ሙያተኞች በአፍሪካ የደኅንነት ጉዳዮችና በአፍሪካዊ መፍትሔዎች ልምድና ዕውቀታቸውን የሚያካፍሉበት ዝግጅትም ተጠባቂ የፎረሙ የመርሃ ግብር አካል ነው። በፎረሙ ላይ በመሪዎችና በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ደረጃ በአህጉራዊና ዓለም አቀፍ ተቋማት ልዩ መልዕክተኞች ምክክር እንደሚካሄድ ተገልጿል።
በቀጣናው መደበኛ ያልሆነ ፍልሰትን ለመከላከል የተጀመሩ የቅንጅት ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ኢጋድ
Oct 20, 2025 551
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 10/2018 (ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) በቀጣናው የሚታየውን መደበኛ ያልሆነ ፍልሰት ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር የጀመራቸውን የተቀናጀ ምላሽ የመስጠት ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታወቀ። የኢጋድ ሶስተኛው የሰራተኛ፣ ስራ እና የሰራተኛ ፍልሰት የሚኒስትሮች ስብሰባ ዛሬ በኬንያ ናይሮቢ ተጀምሯል። “በኢጋድ ቀጣና ብልጽግናን ለማረጋገጥ የሰራተኛ ፍልሰት እና የሰዎች ዝውውር ህጋዊ ማዕቀፍን ማሻሻል” የስብሰባው መሪ ቃል ነው። በስብሰባው ላይ የኢጋድ አባል ሀገራት የሰራተኛ፣ የሀገር ውስጥና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች፣ ባለሙያዎች፣ ዓለም አቀፉ የፍልሰት ድርጅት(አይኤልኦ)፣ ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት(አይኦኤም)፣ የአውሮፓ ህብረትና የልማት አጋሮች ተገኝተዋል። በኢጋድ ቀጣና የሰራተኛ፣ ስራ እና የሰራተኛ ፍልሰት ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ፣ በቀይ ባህር መስመር ያለውን መደበኛ ያልሆነ ፍልሰት መከላከል በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ውይይት ይካሄዳል። በስብሰባው ላይ ከኢጋድ ቀጣና ውጪ የሚገኙ ዜጎች አባል ሀገራትን በነጠላ የመግቢያ ቪዛ መጎብኘት የሚያስችላቸውን የቪዛ ኢኒሼቲቭ ይፋ ይደረጋል። ኢኒሼቲቩ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስርና ድንበር ተሻጋሪ ንግድን ማሳለጥ እንዲሁም ቱሪዝምን የማሳደግ ፋይዳ እንዳለው ኢዜአ ከኢጋድ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። በአውሮፓ ህብረት የፋይናንስ ድጋፍ የሚተገበረው ነጻ የሰዎችና የቁም እንስሳት እንቅስቃሴ የህግ ማዕቀፍ ሁለተኛ ምዕራፍ ይፋ ይሆናል። ማዕቀፉ ህጋዊ የፍልሰት መንገዶች ለማጠናከር እና ቀጣናዊ ትስስርን የማሳካት ግብ ያለው መሆኑንም አመልክቷል። ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር ሰንሰለትን መበጣጠስ፣ በፍልሰት በሌላ ሀገር የሚገኙ ዜጎች ደህንነታቸው እንዲጠበቅ ምቹ ሁኔታን መፍጠር ላይ ምክክር ያደርጋሉ። በውይይቱ ማብቂያ ሀገራት የጋራ መግለጫ እንደሚያወጡ የሚጠበቅ ሲሆን ደህንነቱ የተጠበቀ መደበኛ ፍልሰት፣ ጠንካራ የሰራተኛ አስተዳደር ስርዓት መፍጠርና ለሰዎች ዝውውር የተቀናጀ ቀጣናዊ ምላሽ መስጠት ላይ የጋራ ቁርጠኝነታቸውን እንደሚገልጹ ተጠቁሟል። ኢጋድ በቀጣናው የሚታየውን መደበኛ ያልሆነ ፍልሰት ለመከላከል ከባለድርሻ አካላት ጋር የጀመራቸውን የጋራ ስራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አመልክቷል። ዜጎች ህጋዊ አማራጮችን እንዲከተሉና የኢኮኖሚ ፈተናን ጨምሮ ለሌሎች ገፊ ምክንያቶች ዘላቂ መፍትሄ መስጠት በትኩረት እየተሰራበት እንደሚገኝ ገልጿል። ስብሰባው ጥቅምት 10 እና 11 በባለሙያዎች፣ ጥቅምት 12 ቀን 2018 ዓ.ም በሚኒስትሮች ደረጃ ይካሄዳል።
የአፍሪካ ሀገራት ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት ፕሮግራምን በቁርጠኝነት ሊተገብሩ ይገባል- የአፍሪካ ህብረት
Oct 19, 2025 513
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 8/2018 (ኢዜአ)፦የአፍሪካ ሀገራት ሁሉን አቀፍ የአፍሪካ የግብርና ልማት ፕሮግራም (ካዳፕ) አፈጻጸም ውጤታማነት ለማሳደግ በትኩረት እንዲሰሩ የአፍሪካ ህብረት አሳሰበ። ስድስተኛው የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ መደበኛ ስብስባ ከጥቅምት 11 እስከ 14 ቀን 2018 ዓ.ም በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ይካሄዳል። በስብሰባው ላይ ሚኒስትሮች፣ ባለሙያዎች እና የልማት አጋሮች ይሳተፋሉ። የአፍሪካ የግብርና ኢኒሼቲቮች አፈጻጸም መገምገም እና ዘርፉ ሁሉን አቀፍና ዘላቂ ማድረግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ መምከር የስብሰባው አላማ ነው። እ.አ.አ በ2023 በአዲስ አበባ የተካሄደውን አምስተኛው የልዩ ኮሚቴ ስብሰባ ውጤቶች ግምገማ ይደረጋል። የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት ፕሮግራም (ካዳፕ) የማላቦ ድንጋጌ (ከእ.አ.አ 2014 እስከ 2025) ስኬቶች እና የካዳፕ የካምፓላ ድንጋጌ (ከእ.አ.አ 2026 እስከ 2035) አፈጻጸም ላይ ውይይት ይካሄዳል። የስርዓተ ምግብን ማጠናከር፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር የግብርና ምርታማነት ስርዓት መዘርጋት፣ የበካይ ጋዞችን ልህቀት መቀነስ እና ዘላቂ የውሃና ተፈጥሮ ሀብቶች አስተዳደርን ማጠናከር ሌሎች የምክክር አጀንዳዎች ናቸው። በአፍሪካ በገጠር አካባቢ የሚኖሩ ዜጎችን ኑሮ በማሻሻል ዘላቂ እድገትን ማምጣት በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይ ምክረ ሀሳቦች ይቀርባሉ። ውይይቱ እ.አ.አ በ2026 በአዲስ አበባ የሚካሄዱትን የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባና የህብረቱ የመሪዎች ጉባኤ የሚሆኑ አጀንዳዎችን እንደሚያዘጋጅ ተመላክቷል። የአፍሪካ ህብረት ግብርና፣ የገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር አጀንዳ 2063 ለማሳካት ቁልፍ ሚና የሚጫወቱ ዘርፎች መሆናቸውን አመልክቷል። ህብረቱ የግብርና እና የገጠር ልማት የበለጠ ለማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ አመልክቷል። የህብረቱ አባል ሀገራት የአፍሪካ ሁሉን አቀፍ የግብርና ልማት ፕሮግራምን በተጠናከረ ሁኔታ እንዲተገብሩ ጥሪ አቅርቧል። ስድስተኛው የአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ ጥቅምት 11 እና 12 እንዲሁም ጥቅምት 14 በሚኒስትሮች ደረጃ እንደሚከናውን ኢዜአ ከህብረቱ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የአፍሪካ ህብረት የገጠር ሴቶችን ኑሮ ለመቀየር የጀመራቸውን ጥረቶች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጸ
Oct 15, 2025 503
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 5/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት የገጠር ሴቶችን ኑሮ ለመቀየር እና በአህጉሪቷ የማካካሻ ፍትህን ለማረጋገጥ በበለጠ ቁርጠኝነት እንደሚሰራ አስታወቀ። ዓለም አቀፍ የገጠር ሴቶች ቀን በአፍሪካ ደረጃ ዛሬ በአህጉሪቷ መዲና አዲስ አበባ ዛሬ ይከበራል።   “የገጠር ሴቶችን በማካካሻ ፍትህ አማካኝነት ማብቃት፤ በአፍሪካ ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ ስርዓተ ምግብን ማረጋገጥ” የቀኑ መሪ ሀሳብ ነው። በቀኑ አከባበር ላይ የአፍሪካ ህብረት አመራሮች፣ የመንግስታት ተወካዮች፣ የገጠር ሴቶች አመራሮች እና ተወካዮች፣ የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት፣ የዳያስፖራ ተወካዮች፣ የልማት አጋሮች እና የግሉ ዘርፍ ተዋንያን ይሳተፋሉ። የቀኑ አከባበር አካል የሆነ የቴክኒክ ውይይት ትናንት የተካሄደ ሲሆን የአፍሪካ የገጠር ሴቶች መሪዎች፣ ፖሊሲ አውጪዎች እና ባለሙያዎች ሴቶችን ለማብቃት በየሀገራቱ እየተተገበሩ ያሉ ኢኒሼቲቮችን አስመልክቶ የእውቀት እና የተሞክሮ ልውውጥ አድርገዋል። ዛሬ በሚኖረው ዋናው የቀኑ አከባበር የከፍተኛ ባለስልጣናት ቁልፍ ንግግሮች፣ የፓናል ውይይቶች፣ የገጠር ሴቶች ኢኒሼቲቭ የተሞክሮ ማጋራት መርሃ ግብሮች እና አውደ ርዕዮች ይካሄዳሉ። ሁነቶቹ የገጠር ሴቶች በትምህርት፣ ቴክኖሎጂ እና በግብርና መካናይዜሽን አማካኝነት የሚበቁባቸው የኢኖቬሽን አማራጮች የሚቀርቡባቸው ናቸው። ዓለም አቀፍ የገጠር ሴቶች ቀን ከአፍሪካ ህብረት የ2025 መሪ ሀሳብ ከሆነው “የማካካሻ ፍትህ ለአፍሪካውያን እና ለዘርዓ አፍሪካውያን” የተሳሳረ መሆኑ ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የማሻሻሻ ፍትህ በአፍሪካ ሁሉን አቀፍ እና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ የሚያስችል አካሄድ መሆኑን አመልክቷል።   የቀኑን አከባበር ተከትሎ የጋራ አቋም መግለጫ ይወጣል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን የጋራ መግለጫው አፍሪካ ስርዓተ ጾታን ባማከለ የግብርና ትራንስፎርሜሽን ስራ፣ የገጠር ሴቶችን በማብቃት እንዲሁም ማካካሻ ፍትህ እኩልነት የተረጋገጠበትና የማይበገር ስርዓተ ምግብ ለመገንባት ያላትን የጋራ ቁርጠኝነት የሚያመላክት እንደሆነ ተገልጿል። የዓለም የገጠር ሴቶች ቀን የአፍሪካ ህብረት የስርዓተ ጾታ እኩልነት ለማረጋገጥ እና በማካካኛ ፍትህ አማካኝነት በገጠሪቷ የአፍሪካ አካባቢዎች የሚገኙ ሴቶችን ለማብቃት ያለውን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ገልጿል። ህብረቱ ቀኑን ሲያከብር የበለጸገች፣ ሁሉን አቃፊ እና ዘላቂነትን ያረጋገጠች አህጉር ለመገንባት ባለው መሻት ውስጥ ሴቶች እና ሌሎች የማህበረሰብ ክፍሎች ወደኋላ እንዳይቀሩ ዳግም ቃል ኪዳኑን የሚያድስበት እንደሆነ አመልክቷል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት እ.አ.አ በ2007 ባደረገው ጠቅላላ ጉባኤ ባፀደቀው የውሳኔ ሀሳብ ቁጥር 62/136 አማካኝነት ዓለም አቀፍ የገጠር ሴቶች ቀን እ.አ.አ ኦክቶበር 15 እየተከበረ ይገኛል። ቀኑ በገጠር የሚገኙ ሴቶች ለግብርና፣ ምግብ ዋስትና መረጋገጥ እና ዘላቂ ልማት ያላቸው ወሳኝ አበርክቶዎች የሚዘከርበት ነው።
የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣናን በሙሉ አቅም መተግበር ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ ነው - መሐመድ አሊ ዩሱፍ
Oct 10, 2025 611
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 30/2018 (ኢዜአ)፡- የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣናን ሙሉ ለሙሉ ገቢራዊ ማድረግ ጊዜ የማይሰጠው አንገብጋቢ ጉዳይ ነው ሲሉ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። 24ኛው የምስራቅና ደቡብ አፍሪካ አገራት የጋራ ገበያ (ኮሜሳ) የመሪዎች ጉባኤ በኬንያ ናይሮቢ እየተካሄደ ነው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር ዓለም አቀፍ የኢኮኖሚ ሁነቶች በአፍሪካ የኢኮኖሚ እድገት እና ተወዳዳሪነት ተጽእኖ እያሳደሩ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ይህም ከመቼው ጊዜ በላይ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ሙሉ ለሙሉ በአፋጣኝ መተግበር እንደሚገባው የሚያመላክት ነው ብለዋል። ሊቀ መንበሩ የአፍሪካ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ማህበረሰቦች ከቀረጥ ጋር ያልተያያዙ የንግድ ገደቦችን በማንሳት እና በአፍሪካ ሀገራት መካከል የተሳለጠ የንግድ ልውውጥ ማድረግ የሚያስችሉ ማዕቀፎችን በመተግበር ለአጀንዳ 2063 መዋቅራዊ ትራንስፎርሜሽን ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ አሳስበዋል። የኮሜሳ፣ የደቡብ አፍሪካ የልማት ማህበረሰብ (ሳዴቅ) እና የምስራቅ አፍሪካ ማህበረሰብ (ኢኤሲ) የሶስትዮሽ ትብብር ማዕቀፍ መሆኑን ጠቅሰው፤ ማዕቀፉ የትስስር አጀንዳ ተምሳሌት እና አንድ የሆነች፣ የበለጸገች እና ራሷን የቻለች አህጉር ለመፍጠር የተጀመረውን ጉዞ የተስፋ ብርሃን ፈንጣቂ መሆኑን ተናግረዋል። የአፍሪካ ህብረት ከቀጣናዊ የኢኮኖሚ ማህበረሰቦች ጋር ጠንካራ ትብብር በመፍጠር ቀጣናዊና አህጉራዊ የትስስር አጀንዳዎችን ትግበራ ለማፋጠን በቁርጠኝነት እንደሚሰራ መግለጻቸውን ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
ኢጋድ እና ጀርመን በፍልሰት አስተዳደር እና አየር ንብረት ለውጥ መከላከል ያላቸውን ስትራቴጂካዊ አጋርነት እንደሚያጠናክሩ ገለጹ
Oct 10, 2025 488
አዲስ አበባ፤ መስከረም 30/2018 (ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) እና ጀርመን በፍልሰት አስተዳደር እና አየር ንብረት ለውጥ መከላከል ያላቸውን የቆየ ስትራቴጂካዊ አጋርነት የበለጠ ለማጎልበት እንደሚሰሩ አስታወቁ። ጀርመን ለኢጋድ ቀጣና የተለያዩ የፋይናንስ ድጋፍ ማዕቀፎችንም ይፋ አድርጋለች። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) እና ጀርመን በልማት ትብብራቸው ዙሪያ በጅቡቲ ስትራቴጂካዊ ምክክር አድርገዋል።   በምክክሩ ላይ የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)፣ የጀርመን የኢኮኖሚ ትብብር እና ልማት ሚኒስቴር የምስራቅ አፍሪካ ዘርፍ ኃላፊ ሃኒንግ እና በጅቡቲ የጀርመን አምባሳደር ሄይከ ፉለር (ዶ/ር) ተገኝተዋል። ስትራቴጂካዊ ምክክሩ ሁለቱ ወገኖች በአፍሪካ ቀንድ ባሉ ጉዳዮች ላይ ያላቸውን ትብብር የገመገሙ ሲሆን በቀጣይ የግንኙነት ማዕቀፎች ላይም መክረዋል። ፍልሰት እና አየር ንብረት ለውጥ የውይይቱ አበይት ማጠንጠኛዎች ናቸው። ሁለቱ ወገኖች የጀርመን ቀጣናዊ የፍልሰት ፈንድ ዳግም ማዋቀር ሂደት መልካም ደረጃ ላይ እንደሚገኝ በማንሳት የኢጋድ የቀጣናዊ የፍልሰት ፖሊሲ ማዕቀፍ ፣ የነጻ እንቅስቃሴ የህግ ማዕቀፎች እና የዜጎችን የአኗኗር ሁኔታ የማጠናከር ስራ ለመደገፍ የጋራ ስምምነት ላይ ተደርሷል። ጀርመን ለኢጋድ የፍልሰት ፖሊሲ ትግበራ ፕሮጀክት ቀጣይ ምዕራፍ ትግበራ 2 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዩሮ ለመደገፍ ቃል መግባቷን ኢዜአ ከቀጣናዊ ተቋሙ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። በተጨማሪም ጀርመን በኢጋድ አባል ሀገራት ለሚከናወኑ የማይበገር የአየር ንብረት ለውጥ አቅም ግንባታ ስራዎች በቀጣናዊ የአደጋ ፋይናንስ ፕሮግራም አማካኝነት 22 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዩሮ ለመደገፍ መዘጋጀቷ ተመላክቷል። የፋይናንስ ማዕቀፉ የአየር ንብረት ለውጥ ድንገተኛ አደጋዎችን የመከላከል ስራዎች የሚደገፍ እና የኢጋድ የድርቅ አደጋን የመቋቋም እና ዘላቂነት ኢኒሼቲቭ ጨምሮ ሌሎች ፕሮጀክቶችን የሚደግፍ ነው። በስትራቴጂካዊ ምክክሩ ሁለቱ ወገኖች ውጤት ተኮር፣ አሳታፊ እና ተጠያቂነትን መሰረት ያደረገ አጋርነትን መፍጠር እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። ኢጋድ እና ጀርመን ትብብራቸውን ለማጠናከር፣ የጋራ ስራዎቻቸው የአባል ሀገራት የቅድሚያ ትኩረቶች ያማከሉ እንዲሆኑና የፖሊሲ ምክክራቸውን በመደበኛነት ለማከናወን ከስምምነት ላይ ደርሰዋል። ኢጋድ እና ጀርመን 37 ዓመታትን ያስቆጠረ አጋርነት እንዳላቸው መረጃዎች ያመለክታሉ።
የአፍሪካ ህብረት የወጣቶችን ተሳትፎ እና ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራውን አጠናክሮ ይቀጥላል
Oct 7, 2025 575
አዲስ አበባ፤ መስከረም 27/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት የአህጉሪቷ ወጣቶችን ተሳትፎ እና ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራውን ይበልጥ ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኑን አስታወቀ። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሐመድ አሊ ዩሱፍ ከፓን አፍሪካ የወጣቶች ህብረት ከፍተኛ አመራሮች ከሆኑት ዲያላ ሞሙኒ እና አህመድ ቤኒንግ ጋር በአዲስ አበባ ውይይት አድርገዋል። ውይይቱ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና የፓን አፍሪካ ወጣቶች ህብረት በትብብር መስራት የሚያስችላቸውን የጋራ መግባቢያ ሰነድ ተፈራርመዋል።   የአፍሪካ ህብረት የወጣቶች ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ ሊቀ መንበር ኡቺዚ ምካንዳዋየር በስምምነት ስነ ስርዓቱ ላይ ተገኝተዋል። የአፍሪካ ህብረት ስምምነቱ የአህጉሪቷ ወጣቶች ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እና ወጣቶችን ለማብቃት ያለውን ቁርጠኝነት እንደሚያሳይ ገልጿል። በስምምነቱ አማካኝነት የፓን አፍሪካ የወጣቶች ህብረት በሀገራት ደረጃ ያሉ የወጣት ምክር ቤቶች የሚያቀናጅ አህጉራዊ ማዕቀፍ እና ለአፍሪካ ወጣቶች እንደ ጋራ ድምጽ ሆኖ የሚያገለግል መሆኑን ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የፓን አፍሪካ የወጣቶች ህብረት የፓን አፍሪካ ወጣቶች ህብረት ንቅናቄ የወለደው አህጉራዊ አደረጃጀት ሲሆን እ.አ.አ በ1962 የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች በጊኒ ኮናክሪ ባደረጉት ስብስባ ህብረቱን አቋቁመዋል።   ህብረቱ የተመሰረተው በወቅቱ ወጣቶች አፍሪካ ከቅኝ ግዛት እንድትላቀቅ ለነበረው ትግል አቅም እንዲሆኑ ከማሰብ የመነጨ ነው። የወጣቶች ህብረቱ እንቅስቃሴ የፖለቲካ ድጋፍን በማሰባሰብ እና የአፍሪካ ሀገራት ከቅኝ ግዛት ነጻ እንዲወጡ በማድረግ ረገድ ስትራጂካዊ ሚናውን ተጫውቷል። የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት እ.አ.አ በ2006 ባደረገው ስብስባ የፓን አፍሪካ ወጣቶች ህብረት በድጋሚ የማደራጀት የውሳኔ ሀሳብ በማፅደቅ ህብረቱ የአህጉሪቷ የወጣት መዋቅር እንዲሆን በይኗል።
ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ አፍሪካ በዓለም መድረክ ፍትሃዊ ውክልና እንዲኖራት ድጋፉን ሊሰጥ ይገባል- አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ
Sep 24, 2025 1025
አዲስ አበባ፤ መስከረም 14/2018(ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ አፍሪካ በዓለም መድረክ ፍትሃዊ ውክልና እንዲኖራት እያደረገችው ላለው ጥረት ድጋፍ እንዲሰጥ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ ጥሪ አቀረቡ። 80ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ ከጳጉሜን 4 ቀን 2017 ዓ.ም አንስቶ በድርጅቱ ዋና መቀመጫ ኒውዮርክ እየተካሄደ ይገኛል። የጠቅላላ ጉባኤው አካል የሆነ ከፍተኛ የምክክር እና ክርክር መድረክ ዛሬ በኒው ዮርክ ተጀምሯል። “'ደህናነት በአብሮነት፤ 80 ዓመታት እና ከዚያ በላይ ለሰላም፣ ለልማት እና ለሰብዓዊ መብቶች ጥበቃ” በሚል መሪ ሀሳብ ነው ጉባኤው የሚካሄደው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ “እየተለወጠ ባለው የዓለም የፖለቲካ ስርዓት ውስጥ የአፍሪካ ምልከታዎች” በሚል መሪ ሀሳብ ለጉባኤው ተሳታፊዎች የቪዲዮ መልዕክት አስተላልፈዋል። አምባሳደር ሳልማ በመልዕክታቸው አፍሪካ በተለያዩ መስኮች ራሷን ለመቻል እያከናወነቻቸው ያሉ ስራዎች ፍሬ እያፈሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። አፍሪካ የደህንነት ጉዳዮች በራሷ ፋይናንስ በማድረግ ረገድ ለውጥ ማምጣቷን በማሳያነት ጠቅሰው የአፍሪካ የሰላም እና ደህንነት ማዕቀፍ በአፍሪካውያን ገንዘብ እና ባለቤትነት እየተመራ እንደሚገኝም አመልክተዋል። የአፍሪካ ህብረት የሰላም ፈንድ በአፍሪካውያን በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ በትግበራ ላይ መሆኑን አንስተዋል። አምባሳደሯ በአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ላይ ያላቸውን ሀሳብ ያጋሩ ሲሆን የንግድ ቀጣናው ዜጎች እና ገበያን ከማስተሳሰር ባለፈ ሰው ሰራሽ ድንበሮች በእኛ ላይ ከመጫናቸው በፊት የነበረውን የንግድ ትስስር እና ትብብር እንደሚመለስ ተናግረዋል። አፍሪካ በዓለም አቀፍ የዲፕሎማሲ መድረክ ያላት ድርሻ እያደገ መምጣቱን ገልጸው አህጉሪቷ በቡድን 20 ቋሚ መቀመጫ ማግኘቷ አበይት ማሳያ ነው ብለዋል። አፍሪካ በቡድን 20 ውስጥ ያገኘችው ቋሚ መቀመጫ ለዓለም ችግሮች መፍትሄ ያላትን አይተኬ ሚና በግልጽ የሚያመላክት እንደሆነም ተናግረዋል። እየተለወጠ ያለው የዓለም ስርዓት ለአፍሪካ በርካታ እድሎችን ይዞ መጥቷል ያሉት ምክትል ሊቀመንበሯ ይህን መልካም አጋጣሚ ለመጠቀም እየተሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል። አምባሳደር ማሊካ ዓለም አቀፍ አጋሮች አፍሪካ የዓለም የፋይናንስ ስርዓት እኩልነት የሰፈነበት እንዲሆን እና በተባበሩት መንግስታት የጸጥታ ምክር ቤት ውክልና እንድታገኝ እያነሳች ያለው ፍትሃዊ ጥያቄ እና እውነተኛ መሻት እንዲደግፍ ጥሪ ማቅረባቸውን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። አፍሪካ ከዓለም ጋር ያላት ትብብር በጋራ መከባበር እና የጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ሊሆን እንደሚገባ ገልጸው አፍሪካ ስታድግ የዓለም ብልጽግና እና መረጋጋት ይረጋገጣል ሲሉም ተናግረዋል።
አባል ሀገራት ከመቼውም ጊዜ በላይ አብሮነታቸውን በማጠናከር የተሻለች ዓለም ለመፍጠር በጋራ መሥራት አለባቸው- አንቶኒዮ ጉቴሬዝ
Sep 23, 2025 786
አዲስ አበባ፤ መስከረም 13/2018 (ኢዜአ)፡- የተባበሩት መንግሥታት አባል ሀገራት ከመቼውም ጊዜ በላይ አብሮነታቸውን በማጠናከር የተሻለች ዓለም ለመፍጠር በጋራ መሥራት እንዳለባቸው ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ገለጹ። 80ኛው የተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ጉባዔ በይፋ ተከፍቷል።   በፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድንም በ80ኛው የተባበሩት መንግሥታት ጠቅላላ ጉባዔ ላይ እየተሳተፈ ነው። በመክፈቻ ሥነ-ሥርዓቱ ላይም የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ንግግር አድርገዋል። በንግግራቸውም፤ አባል ሀገራት ከመቼውም ጊዜ በላይ አብሮነታቸውን በማጠናከር የተሻለች ዓለም ለመፍጠር በጋራ መሥራት እንደሚገባቸው አሳስበዋል።   የተባበሩት መንግሥታትን ሥርዓትና መዋቅር ለ21ኛው ክፍለ ዘመን በሚመጥን ልክ መለወጥ እንደሚገባም በአጽንኦት ገልጸዋል። የዓለም ኀብረተሰብ ምርጫውን ሠላም፣ ፍትሕ ዘላቂ ልማት እና ሰብዓዊ ክብር ሊያደርግ እንደሚገባ አስገንዝበው፤ ለተግባራዊነቱም ቁርጠኝነትን እንዲያሳይ ጥሪ አቅርበዋል።
ኢጋድ እና የአውሮፓ ህብረት በተለያዩ መስኮች ያላቸውን አጋርነት ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ
Sep 22, 2025 780
አዲስ አበባ፤ መስከረም 12/2018 (ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) እና የአውሮፓ ህብረት በተለያዩ መስኮች ያላቸውን አጋርነት የበለጠ ለማጎልበት እንደሚሰሩ አስታወቁ። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ምክትል ዋና ፀሐፊ መሐመድ አብዲ ዋሬ ከአዲሱ የአውሮፓ ህብረት የትብብር ኃላፊ ጌራልድ ሃልተር ጋር በጅቡቲ ተወያይተዋል። ውይይቱ ኢጋድ እና የአውሮፓ ህብረት በሰላም፣ ደህንነት፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም ግንባታ፣ የምግብ ዋስትና እና በስደተኞች ጉዳይ ላይ ያላቸውን ትብብር ማጠናከር ላይ ያተኮረ ነው። ሁለቱ ወገኖች አጋርነታቸውን ለማጠናከር እንደሚሰሩ መግለጻቸውን ኢዜአ ከኢጋድ ሴክሬታሪያት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። ኢጋድ እና የአውሮፓ ህብረት እ.አ.አ 2008 አጋርነት መመስረታቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ። ሁለቱ ተቋማት እ.አ.አ ሜይ 2025 ላይ በጅቡቲ የጋራ ምክክር ያደረጉ ሲሆን በተለያዩ መስኮች ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር ከስምምነት ላይ ደርሰዋል።
አፍሪካውያን ለአህጉራቸው ሰላም እና ብልጽግና ያላቸውን ቁርጠኝነት ዳግም ሊያረጋግጡ ይገባል - መሐሙድ አሊ ዩሱፍ 
Sep 9, 2025 1341
አዲስ አበባ፤ ጳጉሜን 4/2017(ኢዜአ)፦ አፍሪካውያን ለአህጉራቸው ሰላም እና ብልጽግና ያላቸውን ቁርጠኝነት በማጽናት የተሻለ መጻኢ ጊዜን ለመፍጠር በጋራ እንዲሰሩ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ጥሪ አቀረቡ። የአፍሪካ ህብረት ቀን ዛሬ እየተከበረ ይገኛል። ቀኑ የአፍሪካ ህብረት እ.አ.አ ሴፕቴምበር 9/1999 በሲርት ድንጋጌ አማካኝነት የተቋቋመበት ቀን የሚታወስበት ነው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ቀኑን አስመልክቶ ባስተላለፉት መልዕክት አፍሪካውያን ቀኑን ሲዘክሩ የአህጉሪቷን ለውጦች በማክበር እና ለአንድነት፣ ሰላምና ብልጽግና ያላቸውን ቁርጠኝነት ዳግም በማረጋገጥ ሊሆን እንደሚገባ ገልጸዋል። የህብረቱ መመስረት ውሳኔ ለአፍሪካ ትብብር፣ ትስስር እና አጋርነት መሰረት የጣለ ነው ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት ቀን የጋራ ጉዟችንን፣ የህዝባችንን አይበገሬነት እና ያጋመደንን የፓን አፍሪካኒዝም መንፈስ የምናከብርበት ነው ሲሉ ተናግረዋል። ሊቀ መንበሩ በመልዕክታቸው በአፍሪካ በተለያዩ መስኮች የተመዘገቡ ስኬቶችን አንስተዋል። በሰላምና ደህንነት፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና፣ የታዳሽ ኃይል ልማት፣ ዲጂታል ኢኖቬሽንና የወጣቶችን አቅም በመገንባት የተከናወኑ ስራዎች አፍሪካን በዓለም መድረክ ያላት ሚና እንዲያድግ አስተዋጽኦ ማድረጉን ነው ሊቀ መንበሩ የገለጹት። የአፍሪካ ህብረት ለአጋርነት፣ ትስስር እና ዘላቂ ልማት ያለውን ቁርጠኝነት ጠቅሰው መንግስታት፣ ሲቪክ ማህበረሰቡ፣ የግሉ ዘርፍ እና ወጣቱ ፈተናዎችን በጋራ በመሻገር አጀንዳ 2063 ይዞ የመጣችውን እድሎች እንዲጠቀም ጥሪ አቅርበዋል። ሁሉም አፍሪካውያን ክብራቸው ተጠብቆ የሚኖሩባት እና መጻኢ ጊዜያቸው ብሩህ የሆነች አህጉር እጅ ለእጅ በመያያዝ እንገንባ ሲሉ ጥሪ አቅርበዋል።
የአፍሪካ ህብረት እና የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን በአህጉራዊ ትስስር ያላቸውን አጋርነት ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ
Aug 26, 2025 1677
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 20/2017(ኢዜአ)፦የአፍሪካ ህብረት እና የተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (ኢሲኤ) በአህጉራዊ ትስስር አጀንዳ ያላቸውን ትብብር የበለጠ ለማላቅ እንደሚሰሩ አስታወቁ። በተባበሩት መንግስታት ድርጅት እና በዓለም የንግድ ድርጅት(ጄኔቫ) የአፍሪካ ህብረት ቋሚ መልዕክተኛ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) ከተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን (ኢሴኤ) ዋና ፀሐፊ ክላቫር ጋቴቴ ጋር ተወያይተዋል።   ሁለቱ ወገኖች አፍሪካ በዓለም መድረክ አንድ የጋራ ድምጽ እንዲኖራት ማድረግ ያለውን ወሳኝ ጠቃሜታ አጽንኦት ሰጥተው መክረውበታል። የአፍሪካ ህብረት እና ኢሲኤ በንግድ፣ቀጣናዊ ትስስር እና የአፍሪካ የአዕምራዊ ንብረትን የበለጠ አጀንዳ ማራመድ ላይ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር እንደሚሰሩ መግለጻቸውን ኢዜአ ከኢሲኤ ያገኘው መረጃ ያመለክታል።   ግርማ አመንቴ(ዶ/ር) በተባበሩት መንግስታት ድርጅት እና በዓለም የንግድ ድርጅት(ጄኔቫ) የአፍሪካ ህብረት ቋሚ መልዕክተኛ ሆነው በሐምሌ ወር 2017 ዓ.ም መሾማቸው የሚታወስ ነው። የአፍሪካ ህብረት እና ኢሲኤ ትብብራቸውን እ.አ.አ በ1960ዎቹ መግቢያ ላይ መጀመራቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ።
አፍሪካ ህብረት እና ጃፓን ስትራቴጂካዊ አጋርነታቸውን የበለጠ ለማጎልበት በትብብር ይሰራሉ
Aug 24, 2025 1434
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 18 /2017 (ኢዜአ)፦አፍሪካ ህብረት እና ጃፓን ያላቸውን ስትራቴጂካዊ አጋርነታቸውን የበለጠ ለማጎልበት በትብብር እንደሚሰሩ አስታወቁ። ዘጠነኛው የጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም(ቲካድ) በዮካሃማ መካሄዱን ቀጥሏል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ከፎረሙ ጎን ለጎን ከጃፓን ዓለም አቀፍ የትብብር ኤጀንሲ (ጃይካ) ፕሬዝዳንት አኪሂኮ ታናካ (ዶ/ር) ጋር ተወያይተዋል።   የኮሚሽኑ ሊቀ መንበር የጃይካ ከአፍሪካ ህብረት ጋር ያለውን ስትራቴጂካዊ አጋርነት እንዲሁም ኢኮኖሚና ማህበራዊን ጨምሮ በአፍሪካ ቁልፍ ዘርፎች እያደረገ ያለውን ኢንቨስትመንት አድንቀዋል። ሊቀ መንበሩ እና ፕሬዝዳንቱ የአፍሪካ ህብረት እና ጃፓን ያላቸውን የጋራ ትብብር ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆናቸውን ገልጸዋል። ዘጠነኛውን የቲካድ ፎረም መንፈስ ወደ ዘላቂ የኢኮኖሚ ለውጥ በጋራ የመፍጠር ምዕራፍ ማሸጋገር እንደሚገባም አንስተዋል። ከነሐሴ 14 ቀን 2017 ዓ.ም ሲካሄድ የቆየው ፎረም የተለያዩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ዛሬ እንደሚጠናቀቅ ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ፤ የአህጉር በቀል መፍትሄዎች መድረክ 
Aug 23, 2025 1470
በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ አፍሪካውያን የአየር ንብረት በርቀት የሚያዩት ስጋት ሳይሆን የዕለት ተዕለት እውነታቸው ነው። በጎርፍ ምክንያት የሚሞቱ ሰዎች እና ተጠራርገው የሚወሰዱ ንብረቶች፣ በተከታታይ ድርቆች ምክንያት የሚያጋጥመው የምርታማነት መቀነስ የአየር ንብረት ለውጥ ከወለዳቸው ቀውሶች መካከል ይጠቀሳሉ። እነዚህ በተጨባጭ የዜጎችን ኑሮ እየተፈታተኑ ያሉ ችግሮች በአፍሪካ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ስነ ምህዳር ላይ ለውጥ እንዲመጣ አስገድደዋል። የድህነት ምጣኔ እና የተፈናቃይ ዜጎች እየጨመረ መምጣት የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተጽእኖዎችን በተግባር የገለጡ ጉዳዮች ሆነዋል።   አፍሪካ ለዓለም የበካይ ጋዝ ልቀት ከአራት በመቶ በታች ድርሻ ቢኖራትም የአየር ንብረት ለውጥ ጉዳት ከፍተኛ ቀንበር የሚያርፍባት አህጉር ሆናለች። ከሳህል ቀጣና የበረሃማነት መስፋፋት እስከ ምስራቅ አፍሪካ ኃይለኛ ጎርፎች የአህጉሪቷ ዜጎች በጣም ውስን ድርሻ ባላቸው ጉዳይ የቀውሱ ከፍተኛ ሰላባ እየሆኑ ነው። አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ የአስቸኳይ ጊዜ ውስጥ ናት ቢባል ማጋነን አይሆንም። እንደ ዓለም አቀፉ የሚቲዎሮሎጂ ድርጅት መረጃ ከእ.አ.አ 1991 እስከ 2022 ባለው ሶስት አስርት ዓመታት ባሉ እያንዳዱ አስርት ዓመታት በአፍሪካ በአማካይ የ0 ነጥብ 3 ዲግሪ ሴልሺየስ የሙቀት ጭማሪ ተመዝግቧል። እ.አ.አ በ2024 የዓለም ሙቀት በ1 ነጥብ 2 ዲግሪ ሴልሺየስ ጨምሮ በዓለም ታሪክ ከፍተኛው ሙቀት የተመዘገበበት ዓመት ነበር። 2024 በአፍሪካ የሙቀት መጠን 0 ነጥብ 86 በመቶ በመጨመር በአህጉሪቷ ታሪክ ከፍተኛው ሙቀት የተዘመገበበት ዓመት ሆኖም ተመዝግቧል። ከሙቀቱ በአሳሳቢ ሁኔታ መጨመር ባሻገር ድርቅ፣ ጎርፍ እና የምግብ ዋስትና ስጋት ላይ መውደቅ ሌሎች የአፍሪካ አየር ንብረት ለውጥ ፈተናዎች ናቸው። እ.አ.አ 2024 ደቡባዊ አፍሪካ ክፍል በቅርብ አስርት ዓመታት ውስጥ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ድርቅ አጋጥሟታል። በድርቁ ምክንያት ዛምቢያ እና ዚምባቡዌ የሰብል ምርታቸው በ50 በመቶ ቀንሷል። በምስራቅ እና ማዕከላዊ አፍሪካ በቅርብ ጊዜ የተከሰቱ ከባድ ጎርፎች ሚሊዮኖችን አፈናቅለዋል፤ የዜጎች ህይወት አመሰቃቅላዋል መሰረተ ልማቶችንም አውድመዋል። የዓለም አቀፉ ሜትሮሎጂ ድርጅት እና የአፍሪካ ልማት ባንክ መረጃዎች እንደሚያመላክቱት ደግሞ የአየር ንብረት ለውጥ የአፍሪካን ከሁለት እስከ አምስት በመቶ ጥቅል ዓመታዊ ምርት (ጂዲፒ) ወጪ እየወሰደ ይገኛል። አንዳንድ ሀገራት ለአየር ንብረት አስቸኳይ ምላሽ ዘጠኝ በመቶ ጥቅል ሀገራዊ ምርታቸውን ፈሰስ ያደርጋሉ። አፍሪካ በየዓመቱ ከ30 እስከ 50 ቢሊዮን ዶላር ለአየር ንብረት ለውጥ ማጣጣሚያ አቅዶች ትግበራ ቢያስፈልጋትም ከዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ ውስጥ የምታገኘው ገንዘብ ከአንድ በመቶ በታች ነው። የዓለም ሜትሮሎጂ ድርጅት የ2024 የአፍሪካ ሪፖርት የአፍሪካ የግብርና ምርታማነት ከእ.አ.አ 1961 በኋላ በ34 በመቶ መቀነሱን ይገልጻል። የአፍሪካ ሀገራት ከውጭ ሀገራት ምግብ ለመግዛት የሚያወጡት 35 ቢሊዮን ዶላር ዓመታዊ ወጪ እ.አ.አ በ2025 ማብቂያ ወደ 110 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ከፍ እንደሚል ገልጿል። የበረሃማነት መስፋፋት፣ የብዝሃ ህይወት መመናመን፣ የጤና እክሎች፣ መፈናቀል እና የታሪካዊ ቅርሶች አደጋ ላይ መውደቅ አፍሪካ እየገጠሟት ያሉ የአየር ንብረት ለውጥ አሉታዊ ተጽእኖዎች ውጤት ናቸው። አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ ቀውሶች ምላሽ ለመስጠት በየዓመቱ 250 ቢሊዮን ዶላር ቢያስፈልጋትም እያገኘች ያለችው 30 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነው። የአየር ንብረት ለውጥ ስጋት አፍሪካ የጥያቄ አምሮት ኖሮባት የምታነሳው አጀንዳ ሳይሆን የፍትህ እና የህልውናዋ ጉዳይም ጭምር ነው። በአዲስ አበባ ከጳጉሜን 3 እስከ 5 ቀን 2017 ዓ.ም “ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት መፍትሄዎችን ማፋጠን፥ የአፍሪካን አረንጓዴ ልማት በፋይናንስ መደገፍ" በሚል መሪ ሀሳብ የሚካሄደው ሁለተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ጉባኤ አህጉሪቷ እየገጠሟት ካሉ አንገብጋቢ ፈተናዎችን በዘላቂነት መሻገር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ይመክራል። የሀገራት መሪዎች፣ ተመራማሪዎችና ባለሙያዎች፣ የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት፣ ወጣቶች እና የግሉ ዘርፍ በአንድነት ይወያያሉ። በጉባኤው ላይ አረንጓዴ አሻራን ጨምሮ በታዳሽ ኢነርጂ፣ ዘላቂ ግብርና እና ተፈጥሮ ተኮር መፍትሄዎች ጨምሮ በአፍሪካ ያሉ አረንጓዴ የመፍትሄ ሀሳቦች የበለ ማላቅ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ሀገራት ተሞክሯቸውን ያቀርባሉ። አፍሪካ ለአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ስራ በየዓመቱ የሚያጋጥማትን የ220 ቢሊዮን ዶላር የፋይናንስ አቅርቦት ክፍተት መሙላት እና አማራጭ የፋይናንስ ምንጮችን መጠቀም ላይ ምክክር ይደረጋል። በብራዚል ቤለም በሚካሄደው 30ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ 30) ጨምሮ በዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ድርድሮች ላይ የአፍሪካን ፍላጎቶች እና ጥቅሞች ማስጠበቅ የሚያስችል የጋራ እና ጠንካራ አቋም መያዝ ከጉባኤው የሚጠበቅ ውጤት ነው። የአፍሪካ ሀገራት በጉባኤው ላይ የአየር ንብረት ለውጥ ለመከላከል የሚያስችሉ ተጨባጭና መሬት ላይ የወረዱ እቅዶቻቸው ላይ የሚያቀርቡ ሲሆን የገቡትን ቃል ኪዳን ወደ ተግባር መቀየራቸውን የሚከታተል የቁጥጥር ስርዓት ትግባራትን የሚያጠናክሩባቸው መንገዶችን በማቅረብ በአጠቃላይ ተጠያቂነትን ለማስፈን ቃልኪዳናቸውን ዳግም ያድሳሉ።   አፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ችግሮች ገፈት ቀማሽ ሳትሆን የመፍትሄዎች እና የአይበገሬነት ስራዎች ማሳያም ናት። የኢትዮጵያ አረንጓዴ አሻራ እና አከባቢ ጥበቃ ስራዎች፣ የኬንያ የእንፋሎት እና የፀሐይ ኃይል ኢንሼቲቮች እንዲሁም የሞሮኮ ኑር ኦውርዛዛቴ የጸሐይ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት አረንጓዴ ልማት ሊሆን የሚችል ብቻ ሳይሆን በተጨባጭ የሚሳካ መሆኑን አፍሪካ ማረጋገጫ እንደሆነች በግልጽ የሚያመላክት ነው። አፍሪካ ከዓለም ዋንኛ በካይ ጋዝ ለቃቂ ሀገራት ገንዘብ በመጠበቅ ብቻ ሳይሆን ሀገር በቀል የፋይናንስ እና ሀብት ማሰባሰብ አቅማቸውን የበለጠ ማሳደግ ይጠበቅባታል። የአዲስ አበባው ጉባኤም የአፍሪካ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ አቅርቦታቸውን እንዲጨምሩ ጥሪ የሚቀርብበት ነው። አፍሪካውያን እንደ አረንጓዴ አሻራ ያሉ ከንግግር ያለፉ ሀገር በቀል መፍትሄዎችን በመተግበር አይበገሬ አቅም ሊገነቡ ይገባል። የአፍሪካ የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ሀገር በቀል የአየር ንብረት ለውጥ መፍትሄዎችን ከዓለም አቀፍ አጋርነት ጋር ከማዛመድ አኳያ ያላው ሚና ወሳኝ የሚባል ነው። ጉባኤው አፍሪካ ከአየር ንብረት ለውጥ ተጋላጭነት ትርክት ወደ መፍትሄ አፍላቂነት እና የግንባር ቀደም ሚና አበርካችነት ለመሸጋገር እንደ መስፈንጠሪያ የሚያገለግል ትልቅ እድል ነው። የአዲስ አበባው ጉባኤ ከስብስባ ባለፈ አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ ቆርጣ ለተነሳችበት የተግባር ምላሽ ጉዞ እና የዓለም አቀፍ ተጠያቂነት መረጋገጥ የጋራ ትግል ውስጥ ትልቅ እጥፋት ሊሆን ይችላል።  
በመልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ የአንድ ሀገር የመልማት እና የማደግ ፍላጎት ሊገደብ አይገባም - አንቶኒዮ ጉቴሬዝ
Aug 5, 2025 1496
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 28/2017(ኢዜአ)፦መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ የአንድን ሀገር የመልማት እና የማደግ መብት በፍጹም መወሰን የለበትም ሲሉ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ገለጹ። ሶስተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የባህር በር የሌላቸው በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት ኮንፍረንስ ዛሬ በተርኪሚኒስታን መካሄድ ጀምሯል።   በኮንፍረንሱ ላይ ኢትዮጵያን ጨምሮ በአፍሪካ፣እስያ፣አውሮፓ እና ደቡብ አሜሪካ የሚገኙ 32 ሀገራት ተሳታፊ ሆነዋል። ከተሳታፊዎቹ ሀገራት መካከል 16 ከአፍሪካ ናቸው። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በኮንፍረንሱ ላይ ባደረጉት ንግግር የባህር በር የሌላቸው ሀገራት ያሉባቸውን የልማት፣የኢኮኖሚ እና የእድገት ፈተናዎችን አንስተዋል። በማደግ ላይ የሚገኙ የባህር በር የሌላቸው ሀገራት የመልማት አቅማቸው ባሉበት መልክዐ ምድራዊ ስፍራ ምክንያት ሊገደብ እንደማይገባ አመልክተዋል። ዋና ፀሐፊው የባህር በር የሌላቸው ሀገራት የዓለምን ሰባት በመቶ ህዝብ የያዙ ቢሆንም በዓለም ኢኮኖሚና ንግድ ውስጥ ያላቸው ድርሻ ከአንድ ፐርሰንት ጥቂት ሻገር ያለ መሆኑን ገልጸው ይህ ትልቅ ኢ-ፍትሃዊነት ነው ሲሉ ተናግረዋል። በተጨማሪም ሀገራቱ ለአየር ንብረት ለውጥ ያላቸው ድርሻ ዝቅተኛ ቢሆንም የጉዳቱ ዋንኛ ሰለባ መሆናቸውን አንስተዋል። የዓለም ማህበረሰብ ሀገራቱ በዓለም ኢኮኖሚ እና የንግድ ስርዓት ውስጥ ያላቸው ድርሻ እንዲያድግ ድጋፍ እንዲያደርግ ጠይቀዋል።   የባህር በር የሌላቸው ሀገራት በዓለም የንግድ እሴት ሰንሰለት ውስጥ ያላቸውን ተሳትፎ እንዲጨምር የሚያስችል መዋቅራዊ ለውጥ ያሻል ያሉት ዋና ፀሐፊው፥ ይህም ሀገራት ጥሬ ምርቶችን ከመላክ ከፍተኛ እሴት ያለው ምርት ወደ ማምረት እንዲሸጋገሩ ያደርጋል ነው ያሉት። የባለብዙ ወገን የልማት ባንኮች እና የፋይናንስ ተቋማት አነስተኛ ወለድ ያለው የፋይናንስ አቅርቦት ለሀገራት ተደራሽ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል። የባህር በር የሌላቸው ሀገራት ከትስስር ጋር በተያያዘ የሚገጥማቸውን የመሰረተ ልማት እና መዋቅራዊ ችግሮች መፍታት እንደሚገባ አመልክተዋል። ለዚህም ድንበር ተሻጋሪ አሰራሮችን ማቅለል፣የተለያዩ የመመዘኛ ደረጃዎችን ማጣጣም እንዲሁም የተሳለጠ ንግድና ትራንዚት እንዲኖር የሚያስችሉ የህግ ማዕቀፎችን ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ነው ያነሱት። ጉቴሬዝ በመሰረተ ልማት መጠነ ሰፊ መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ ይገባል ያሉ ሲሆን የባህር በር የሌላቸው በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት የማይበገር የትራንስፖርት መተላለፊያ መስመር፣ ድንበር ተሻጋሪ የእርስ በእርስ የኢነርጂ ትስስር፣ ሰፊ የአየር ትስስር እና በቴክኖሎጂ የታገዙ የሎጅስቲክስ አውታሮች እንደሚያስፈልጋቸው አስገንዝበዋል። ሀገራቱ ያለባቸውን የመልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ እክሎች ምላሽ ለመስጠት ፍትሃዊ የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነትን ማስፈን እንዳለባቸው አሳስበዋል።   ኮንፈረንሱ ላይ ኢትዮጵያ እና የባህር በር የሌላቸው ሌሎች ሀገራት በዓለም የንግድ ስርዓት ውስጥ ያላቸው ተሳትፎ በትስስር፣ በፍትሃዊ የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነት እና ዓለም አቀፍ ትብብር እንዲያድግ ግፊት እንደሚያደርጉ ተመላክቷል። ሶስተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የባህር በር የሌላቸው በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት ኮንፍረንስ እስከ ነሐሴ 2 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም