ዓለም አቀፍ ዜናዎች
በእስራኤልና ኢራን መካከል የሚታየውን አሳሳቢ ሁኔታ ሀገራት በአስቸኳይ ሊያስቆሙት ይገባል- አንቶኒዮ ጉተሬዝ
Apr 15, 2024 1171
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7/2016(ኢዜአ)፡- አለም ተጨማሪ ጦርነት እንድታስተናግድ እድል ባለመፍጠር በእስራኤልና ኢራን መካከል የሚታየውን አሳሳቢ ሁኔታ ሀገራት በአስቸኳይ ሊያስቆሙት እንደሚገባ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ አሳሰቡ። ኢራን እስራኤል ከሳምንታት በፊት ሶርያ በሚገኘው ቆንስላ ጽሕፈት ቤት ጥቃት አድርሳብኛለች በሚል ባሳላፍነው ቅዳሜ ሌሊት መጠነ ሰፊ ጥቃት መሰንዘሯ በተለያዩ የዓለም መገናኛ ብዙሃን መዘገቡ ይታወሳል። ይህንንም ተከትሎ በቀጣናውና በአለም ሀገራት የተፈጠረውን ከፍተኛ ውጥረት ለማርገብ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ የጸጥታ ምክር ቤቱን አስቸኳይ ስብሰባ ጠርተዋል። በስብሰባውም አለም ተጨማሪ ጦርነት የምታስተናግድበት ምንም አይነት አቅም ስለሌለ ሀገራት በእስራኤልና ኢራን መካከል የሚታየውን አሳሳቢ ሁኔታ በአስቸኳይ ሊያስቆሙት ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። ችግሩ በቸልታ የሚታይ ከሆነ አስከፊ ጉዳት ሊያስከትል እንደሚችል መናገራቸውን ያስነበበው ፍራንስ 24 የጸጥታው ምክር ቤት አባላት ሁኔታውን በአስቸኳይና ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ሊያስቆሙት እንደሚገባ ማሳሰባቸውንም ዘግቧል።
በሞዛምቢክ በደረሰ የጀልባ አደጋ ህጻናትን ጨምሮ ከ90 በላይ ሰዎች ሕይወት አለፈ
Apr 8, 2024 2081
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 30/2016(ኢዜአ)፦በሞዛምቢክ ሰሜናዊ ክፍል የባህር ዳርቻ በተከሰተ የጀልባ አደጋ ህጻናትን ጨምሮ ከ90 በላይ ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተገለጸ። በሞዛምቢክ ሰሜናዊ ክፍል በምትገኘው ናምፑላ ግዛት 130 የሚሆኑ ሰዎችን አሳፍራ ስትጓዝ የነበረች ጀልባ መስጠሟን የሀገሪቱ ባለስልጣናት አስታውቀዋል። ነዋሪዎቹ በግዛቷ የተከሰተውን የኮሌራ ወረርሽኝ በመሸሽ ወደ ሌላ አካበቢ ለመሄድ በጀልባ በተሳፈሩበት ወቅት አደጋው እንደተከሰተ የገለጹት ባለስልጣናቱ ጀልባዋ መሸከም ከምትችለው የሰው መጠን በላይ በመጫኗ አደጋው እንደደረሰ አመልክተዋል። በዚህም ህጻናትን ጨምሮ ከ90 በላይ ሰዎች ሕይታቸው እንዳለፈ ማረጋገጣቸውን ቢቢሲ ዘግቧል። በአሁኑ ወቅት አምስት ሰዎችን ከአደጋው በሕይወት ማትረፍ እንደተቻለ ያመለከተው ዘገባው ተጨማሪ ሰዎችን ለማዳን ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አስነብቧል። የናምፑላ ግዛት ባለፈው አመት በሞዛምቢክ በተከሰተው የኮሌራ ወረርሽኝ ክፉኛ ከተጎዱ አካባቢዎች መካከል አንዷ መሆኗም በዘገባው ተመላክቷል።
የአየር ንብረት ለውጥና መዘዙ
Apr 5, 2024 1378
በዓለማችን ላይ እየተስተዋለ ያለው የአየር ንብረት ለውጥ የተወሳሰበ ችግር እያስከተለ ከመሆኑ በተጨማሪ በስነምህዳር ላይ እያደረሰ ያለው አደጋ ሊቀለበስ ወደ ማይችልበት ደረጃ ላይ እየደረሰ መሆኑን ሞደርን ዲፕሎማሲ ድረገጽ አስነበበ። ድረ ገጹ በዓለማችን በየዓመቱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የአየር ንብረት ለውጥ በሚያስከትለው ድርቅ፣ ጎርፍ እና ተዛማጅ በሆኑ ክስተቶች ምክንያት ቀያቸውን ጥለው ለመሰደድ እንደሚገደዱ አስነብቧል። የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ በይነመንግስታት ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው አሁን ላይ ያለው የዓለማችን የሙቀት መጠን ወደ 1 ነጥብ 5 ዲግሪ ሴሊሺየስ እየተጠጋ በመምጣቱ በስነምህዳር፣ በከባቢ አየር እና በአካባቢ ላይ ከፍተኛ ለውጥ እየተስተዋለ መሆኑን ገልጿል። የአየር ንብረት ለውጥ ለዘላቂ ልማት እንቅፋት በመሆን ተፈጥሮአዊና ሰው ሰራሽ ክስተቶች የሚፈጥራቸውን ችግሮች በማባባስ ለሰዎች መፈናቀልና የህይወት መጎሳቆል እያደረሰ ይገኛል። እንደአውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2020 በማዕከላዊ አሜሪካ እና ደቡባዊ ሜክሲኮ የተከሰተው ሃሪኬን ኤታ የተባለው የአየር ንብረት ለውጥ ክስተት ያስከተለው የሰብል ውድመትና የመሰረተ ልማት አውታሮች ላይ የደረሰው አደጋ ከባለፉት ሁለት አስርተ ዓመታት ውስጥ እጅግ የከፋ አደጋ መሆኑን ዘገባው አመልክቷል። በዚህም በጎርፍ፣ በመሬት መንሸራተትና በሰብል ውድመት ምክንያት ከ1 መቶ 20 ሺህ በላይ ሰዎችን ከሞቀ መኖሪያቸው ተፈናቅለው እርዳታ ጠባቂ እንዳደረጋቸው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከፍተኛ የስደተኞች ኮሚሽንን መረጃ ዋቢ አድርጎ አትቷል። የአየር ንብረት ለውጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ መምጣቱን የጠቆመው ድረ ገጹ በቀጣይ ተመሳሳይ ችግሮች ሊያጋጥሙ እንደሚችሉም አመልክቷል። በአውሮፓውያኑ 2022 ወደ 32 ሚሊየን የሚጠጉ ሰዎች በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የተፈናቀሉ ሲሆን፤ ይህ አሃዝ በ2008 ከተከሰተው በ41 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን ዘገባው አመልክቷል። ይህም የዓለማችን የሙቀት መጠን እየጨመረ መምጣቱን እንጂ ምንም ዓይነት የመቀነስ አዝማሚያ ያላሳየ መሆኑን ያመለከተው ዘገባው በቺሊ፣ ካናዳ፣ ዛምቢያ፣ ሞዛምቢክ፣ ሜክሲኮ፣ ኢክዋዶር፣ ሊቢያ እና በሌሎችም አገራት ሃሪኬን በተሰኘው የአየር ለውጥ፣ በሰደድ እሳት፣ በጎርፍ እና በድርቅ ምክንያት ለባለፉት በርካታ ወራት መፈናቀልን እንዳስከተለ ተገልጻል። የአለም ባንክን የትንበያ መረጃ ዋቢ ያደረገው ድረ ገጹ በአውሮፓውያኑ 2050 ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር በተያያዘ 216 ሚሊዮን ሰዎች ሊፈናቀሉ እንደሚችሉ ተመላክቷል። ድረገጹ ይሄ ክስተት የሚያስከትላቸው ችግሮች እንዳይቀጥሉ መቆጣጠር ካስፈለገ ዘላቂ ልማት ላይ ያተኮሩ ግንዛቤን የሚያሳድጉ ትምህርቶች፣ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ እውነተኛ ውይይቶች እና ተፈጥሮን መሰረት ያደረጉ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎች ትኩረት ሊሰጣቸው እንደሚገባ በማሳሰብ መሪዎች የሚጠበቅባቸውን ሊተገብሩ ይገባል ሲል ምክሩን አስቀምጧል።  
በአባቱ የሎተሪ ስጦታ 4 ሚሊዮን ዶላር ያሸነፈው እድለኛ 
Apr 4, 2024 1340
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2016(ኢዜአ)፦ በአሜሪካ ኤሊኖይ ግዛት ነዋሪ የሆነው ግለሰብ አባቱ ያበረከቱለት የሎተሪ ትኬት የ4 ሚሊዮን ዶላር እድለኛ አድርጎታል። ስቴቨን ሪቻርድስ ይባላል በኤሊኖይ የባሪንግተን ከተማ ነዋሪ ሲሆን ከቀናት በፊት ከአባቱ ጋር ቁርስ ለመመገብ ባቀኑበት ምግብ ቤት ከአባቱ ስጦታ ይበረከትለታል። ስጦታውም የ10 ዶላር የሎተሪ ትኬት ነበር። አዛውንቱ ያበረከቱለት የሎተሪ ትኬት ወዲያውኑ ተፍቆ ውጤቱን የሚያሳይ ሲሆን ስቴቨንም ትኬቱን በፋቀበት ቅጽበት ከፍተኛ ድንጋጤ እንደተሰማው ለማሳቹሴት የሎተሪ አስተዳደር ተናግሯል። የሎተሪ ትኬቱ የ4 ሚሊዮን ዶላር እድለኛ እንዳደረገኝ ሳውቅ በድንጋጤ ማመን አልቻልኩም በዚህም ውጤቱን ከመናገሬ በፊት በስልኬ ስካን አደረኩት ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል። በመቀጠለም የአባቱ ስጦታ እድለኛ እንዳደረገው ለባለቤቱ እንዲሁም ለአባቱ መናገሩን ዩፒአይ ዘግቧል። ስቴቨን በሎተሪ ከደረሰው 4 ሚሊዮን ዶላር ውስጥ በተወሰነው ገንዘብ ከባለቤቱ ጋር የተለያዩ አካባቢዎችን ለመጎብኘት ማቀዱን ዘገባው አመልክቷል።
የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት በሱዳን ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ ጥረቱን እንደሚቀጥል አስታወቀ
Apr 3, 2024 870
አዲስ አበባ ፤ መጋቢት 25/2016(ኢዜአ)፡- የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት በሱዳን ያለው ግጭት በዘላቂነት እንዲቆምና ሰላም እንዲመጣ ጥረቱን እንደሚቀጥል አስታወቀ። ምክር ቤቱ የተመሰረተበትን 20ኛ ዓመት በዓል እና ለአዲስ አባል ሀገራት የአቀባበል መርሃ ግብር አካሂዷል። አቀባበል የተደረገላቸው አንጎላ፣ ቦትስዋና፣ ኮትዲቯር፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ግብጽ፣ ኢኳቶሪያል ጊኒ፣ ጋምቢያ፣ ሴራሊዮን፣ ታንዛኒያ እና ኡጋንዳ ናቸው። የአፍሪካ ሕብረት የፖለቲካ ጉዳዮች፣ የሰላምና ጸጥታ ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ባንኮሌ አዲኦዬ በዚህ ወቅት እንዳሉት፥ ምክር ቤቱ በአህጉሪቱ ሰላምና ጸጥታን ለማስፈን ባደረገው ጥረት ለውጥ መምጣቱን ተናግረዋል። የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነትን ለማቆምና ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ የተደረገው የሰላም ስምምነት የምክር ቤቱ የአፍሪካን ችግር በአፍሪካዊ ማዕቀፍ የመፍታት ሂደት ዐቢይ ማሳያ ነው ብለዋል። በምስራቅ አፍሪካ ቀጣና ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲኖር የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጸዋል። ምክር ቤቱ በሱዳን የተከሰተውን ግጭት በማቆም ዘላቂ ሰላም ለማምጣት ጥረት እያደረገ መሆኑንም አንስተዋል። ለዚህም ከአፍርካ ህብረት፣ ከኢጋድና ከጎረቤት ሀገራት ጋር በመሆን ተፋላሚ ሃይላትን የማነጋገርና ወደ ሰላማዊ ውይይት እንዲመጡ እየተሰራ ስለመሆኑ ጠቅሰዋል። በቅርቡ በሚካሄደው የምክር ቤቱ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ስብሰባ የሱዳን ጉዳይ በልዩ ትኩረት ምክክር እንደሚደረግበት ኮሚሽነሩ ጠቁመዋል። በአፍሪካ ግጭቶችን የመፍታትና እንዳይከሰቱ የመከላከል ጥረቶች ውጤታማ እንዲሆኑ የአፍሪካ ህብረት ለሰላምና ጸጥታ ምክር ቤቱ ድጋፍ ማድረጉን እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት በቀይ ባህር አካባቢ የሚስተዋሉ ግጭቶች በምስራቅና ሰሜን የሚገኙ አባል አገራት ላይ የሚያመጣውን ተጽእኖ በመረዳት ከሚመለከታቸው ጋር እንደሚሰራ ጠቁመዋል። ግጭትን አስቀድሞ መከላከል፣ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የሚያስችል አቅምና ትብበር ማጠናከር፣ የዴሞክራሲ ባህልን ማሳደግ ምክር ቤቱ ትኩረት የሚሰጣቸው ተግባራት እንደሆኑ አንስተዋል። የአፍሪካ ህብረት እ.አ.አ ሐምሌ 9/2002 በደቡብ አፍሪካ ደርባን ባካሄደው የመጀመሪያ ጉባኤ የሰላምና ፀጥታ ምክር ቤት ማቋቋሚያ ፕሮቶኮልን ማጽደቁ ይታወቃል። ፕሮቶኮሉ ከታህሳስ 2003 ጀምሮ በከፊል ሲተገበር ቆይቶ ከ2004 የመጀመሪያዎቹ ወራት አንስቶ ሙሉ ለሙሉ ወደ ስራ ገብቷል። የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት እኩል ድምጽ ያላቸው 15 አባል አገራትን የያዘ ሲሆን በአህጉሪቱ ሰላምና ጸጥታ ጉዳይ ላይ የሚሰራ ነው።
ኖርዌይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለመጠቀም የምታካሂደው እንቅስቃሴ በዘርፉ ፈርቀዳጅ ሀገር ሊያደርጋት ይችላል ተባለ
Apr 3, 2024 248
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 25/2016(ኢዜአ)፡- ኖርዌይ በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ረገድ የምታከናውነው ተግባር ተሽከርካሪዎቹን በስፋት በመጠቀም ቀዳሚዋ ሀገር ሊያደርጋት እንደሚችል ተገለጸ። ኖርዌይ ከአውሮፓውያኑ 2025 ጀምሮ የናፍጣና የቤንዚን ተሽከርካሪዎች ወደ ሀገሪቱ እንዳይገቡ ክልከላ ማድረጓ ተዘግቧል። የሃገሪቱ ዜጎች የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን እንዲጠቀሙ ከፍ ያሉ ማበረታቻዎች እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ነው የተዘገበው።   የነዳጅ ተሽከርካሪዎች በሃገሪቱ ላይ ከፍ ያለ የአካባቢና የአየር ብክለት ማስከተላቸው ለዚህ ውሳኔ ገፊ ምክንያት መሆኑን የገለጸው የኖርዌይ መንግስት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በስፋት በዜጎች እንዲዘወተሩ ለማድረግም ከፍተኛ የተባለ የግብር ቅነሳ አድርጓል። የግብር ቅነሳና መሰል ማበረታቻዎች ትርጉም ያለው ለውጥ በማምጣታቸው በሃገሪቱ ጥቅም ላይ ከዋሉት ተሽከርካሪዎች አብዛኞቹ የኤሌክትሪክ ሆነዋል ሲል ዘኢንዲፔንደት ዝግቧል። በሀገሪቱ የሚገኙትን የናፍጣና የቤንዚን ተሽከርካሪዎች ሙሉ ለሙሉ በኤሌክትሪክ ተክቶ ለማጠናቀቅ ጥቂት አመታት መውሰዱ እንደማይቀር በዘገባው ተመልክቷል። የመንግስት ቁርጠኝነት በዚሁ ከቀጠለ ሁሉም የሃገሪቱ ዜጎች የሚጠቀሙባቸው ተሽከርካሪዎች ሙሉ ሙሉ በኤሌክትሪክ የሚተኩ መሆኑን ነው ዘገባው ያተተው። በኖርዌይ የልሂቃን ቡድን የመጓጓዣ ዘርፍ ተመራማሪ ኢንግቪልር ሮርሆልት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ሽያጭ ከ92 በመቶ በላይ ማደጉን አስረድተዋል።   ኖርዌይ የወሰደችው አይነት እርምጃ በሌሎች ሃገራት መተግበር ቢችል አሁን ያለው የነዳጅ ዋጋ ሊረጋጋ ከመቻሉም በላይ የአየርና የአካባቢ ብክለትም ሊቀንስ እንደሚችል ተመልክቷል። ባሳለፍነው የአውሮፓውያን አመት በሃገሪቱ 1 መቶ 5 ሺህ የኤሌክትሪክ እና 76 ሺህ የነዳጅ ተሽከርካሪዎች ተሽጠዋል ተብሏል።
በደቡብ ምስራቅ ብራዚል በጣለ ከባድ ዝናብ በትንሹ ሰባት ሰዎች መሞታቸው ተገለጸ
Mar 25, 2024 418
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2016(ኢዜአ)፦በደቡብ ምስራቅ ብራዚል በጣለ ከባድ ዝናብ በትንሹ ሰባት ሰዎች መሞታቸው ተገልጿል። ከሬዮዴጄኔሮ 65 ኪሎ ሜትሮችን በምትርቀው ፔትሮ ፖሊስ በደረሰው አደጋ በትንሹ ሰባት ሰዎች መሞታቸውንና በርካቶች መቁሰላቸውን የአካባቢው ባለስልጣናት ገልጸዋል። በአደጋው ለ16 ሰዓታት ያክል በጭቃ ተሸፍና ህይወቷን ማትረፍ የተቻለ የአራት ዓመት ታዳጊን ጨምሮ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች ዝናቡን ተከትሎ ከተከሰተው የመሬት መንሸራተት ከ100 በላይ ሰዎችን ማዳናቸውም ተገልጿል። መቀመጫውን በሰሜን አሜሪካ ያደረገው ፒቢኤስ(public broadcasting service) እንደዘገበው ረዘም ላለ ሰዓት በጣለው ዝናብ ምክንያት በከተማዋ የመሬት መንሸራተትን ጨምሮ ቤቶችም ፈራርሰዋል። የከተማው ከንቲባ ክላውዲዮ ካስትሮ እንደገለጹት ካለፈው ሀሙስ ጀምሮ አደጋው ሊከሰት እንደሚችልና ነዋሪዎቹም እንዲጠነቀቁ መልዕክት ተላልፏል። የአደጋ ጊዜ ሰራተኞችም በአደጋው ጉዳት የደረሰባቸውን ዜጎች ለማዳን በአነፍናፊ ውሾች ጭምር በመታገዝ የነፍስ አድን ስራዎችን እያከናወኑ ሲሆን እስከ አሁን አንድ ሰው የደረሰበት እንዳልታወቀ ተገልጿል። የአየር ትንበያ ባለሙያዎች በፔትሮፖሊስ የተከሰተው ከባድ ዝናብ ኤስፒሪቶ ሳንቶ ወደተባለው አጉራባች ክልል ሊገባ እንደሚችልና አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግ አሳስበዋል።
የቻይና- አፍሪካ የንግድ ልውውጥ ዕድገት  
Mar 14, 2024 737
የቻይና አፍሪካ ግንኙነት ባለፉት አስርት አመታት በከፍተኛ ደረጃ እያደገ በመምጣቱ ቻይና በአፍሪካ አህጉር በንግድ፣ በኢንቨስትመንት እና በመሠረተ ልማት ዝርጋታ ዋነኛ ተዋናይ ከሆኑ ሀገራት መካከል አንዷ አድርጓታል። በቻይና እና በአፍሪካ ሀገራት መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ በተያዘው የፈረንጆች ዓመት ከ47 ቢሊዮን ዶላር በላይ መድረሱን የስፑትኒክ ዘገባ ያመለክታል። የንግድ ልውውጡ በፈረንጆቹ አዲስ ዓመት የመጀመሪያዎቹ ሁለት ወራት ብቻ በ13.9 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። ቻይና ወደ አፍሪካ የምትልከው ምርት በ21 በመቶ ማደጉን ያመለከተው ስፑትኒክ በአንፃሩ ቻይና ከአፍሪካ ሀገራት የምታስገባው ምርት መጠን በ4.5 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። በፈረንጆቹ 2021 ይፋ የሆነው የቻይና አፍሪካ ትብብር ራዕይ 2035፤ "በአፍሪካ የተሰራ" የሚሉ ብራንዶችን በመፍጠር እና በማቋቋም ረገድ የአፍሪካ ምርቶች በዓለም ገቢያ ተመራጭ እንዲሆኑ ቻይና እየሠራች እንደሆነ ዘገባው አመልክቷል። የቻይና አፍሪካ 2035 ራዕይ አፍሪካ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን እንድታሳድግ እና ከአለም አቀፍ የኢንዱስትሪ እና የአቅርቦት ሰንሰለት ጋር እንድትተሳሰር ለማድረግ እቅድ እንዳለውም በዘገባው ተጠቁሟል። ባሳለፍነው የፈረንጆቹ 2023 መገባደጃ ላይ ቻይና ኢትዮጵያን ጨምሮ ስድስት የአፍሪካ ሀገራት ምርቶቻቸውን ከቀረጥ ነፃ ወደ ሀገሯ እንዲገቡ መፍቀዷን ያስታወሰው ዘገባው፤ ይህም የአፍሪካ ቻይና የንግድ ትስስርንና ትብብርን ከፍ እንዲል አድርጓል ብሏል። ከአፍሪካ ሀገራት ደቡብ አፍሪካ የቻይና ትልቁ የንግድ አጋር መሆኗን ያመለከተው ዘገባው፤ ናይጄሪያ፣ አንጎላ እና ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እንደቅደም ተከተላቸው የቻይና የንግድ አጋር መሆናቸውን መረጃው ያመለክታል።  
በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎች በኢትዮጵያ 
Mar 14, 2024 766
ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባውን የነዳጅ ፍጆታ ለመቀነስ እና የአየር ብክለትን ለመከላከል የሚደረገውን ሰፊ ጥረት እውን ለማድረግ ኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለህዝብ ማመላለሻ አገልግሎት በማዋል ከፍተኛ እምርታን አስመዝግባለች ይላል የአፍሪካ 24 ድረ ገጽ ዘገባ። በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ላይ እየተዘዋወሩ የሚገኙት የኤሌክትሪክ ሚኒባሶች ድምጽ አልባና ለአካባቢው ተስማሚ መሆናቸውን ያተተው የአፍሪካ 24 ድረ ገጽ ዘገባ፤ ይህ የለውጥ ጅማሮ እየጨመረ በመጣው ፍላጎት እና በመንግስት ጠንካራ ድጋፍ የተገኘ መሆኑን አመልክቷል። መንግስት በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን በረጅም የጊዜ ማእቀፍ ውስጥ ከጎዳናዎች የማስወጣት እቅድ ነድፎ እየሰራበት በመሆኑ ምክንያት አሮጌዎቹን የነዳጅ ተሽከርካሪዎች ተክተው ለዜጎች ንጹህና ጤናማ አገልግሎት የሚሰጡት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ከፍ ያሉ ማበረታቻዎች እየተደረገላቸው መሆኑንም ዘገባው አመልክቷል። ከእነዚህ ማበረታቻዎች መካከልም ለአካባቢ ጥበቃና ለጤና ምቹ ናቸው የተባሉት በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ያለምንም ቀረጥ አሊያም በዝቅተኛ ቀረጥ ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገቡ ወይም በከፊል ገብተው እንገጣጠሙ ማድረግ ተጠቃሽ ነው። እነዚህ ተሽከርካሪዎች ሃገር ውስጥ ገብተው መገጣጠማቸው ለኢትዮጵያውያን የእውቀትና የሙያ ሽግግር ከማድረጋቸው ባለፈ ለወጣት ክፍል የስራ እድሎችን እንደሚፈጥሩ ዘገባው አመልክቷል። በሃገር ውስጥ የተገጣጠሙት ተሽከርካሪዎች የዜጎችን እንቅስቃሴ ከማሳለጥ አኳያም ጉልህ አበርክቶ እንዳላቸውም ጠቁሟል። የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች መስፋፋት ለነዳጅ ግዥ የሚወጣውን ከፍተኛ የሃገር ሃብት ለሌላ ልማት ለማዋልና ከአካባቢ ጥበቃና ከዜጎች ጤና ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያ መንግስት ያለውን ቁርጠኝነት ያሳየበት መሆኑን ያነሳው ዘገባው ተሽከርካሪዎቹ በስፋት ጥቅም ላይ ሲውሉ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ከማሻሻላቸውም ባሻገር ጤናማ የከተሞች ውስጥ እንቅስቀሴ በመፍጠር የአረንጓዴ አሻራ ትልሙን በማሳካት ያግዛሉ ብሏል።
በህንድ አንድ እቃ ጫኝ ባቡር ያለ አሽከርካሪ 70 ኪሎ ሜትሮች መጓዙ ተነገረ
Feb 26, 2024 1121
አዲስ አበባ ፤የካቲት 18/2016 (ኢዜአ)፦በህንድ አንድ እቃ ጫኝ ባቡር ያለ አሽከርካሪ 70 ኪሎ ሜትሮች መጓዙን ተከትሎ የሀገሪቱ የባቡር አስተዳደር ምርመራ እያካሄደ መሆኑን ገልጿል። በህንድ አንድ እቃ ጫኝ ባቡር ያለ አሽከርካሪ መንቀሳቀሱን የሚያሳዩ ምስሎች በማህበራዊ ሚዲያ መሰራጨታቸውን ተከትሎ ጉዳዩ አነጋጋሪ ሆኗል። የህንድ የባቡር አስተዳደር ባለስልጣናት ለመገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ መነሻውን ከካሽሚር ግዛት ወደ ጃሙ ያደረገ እቃ ጫኝ ባቡር ያለ አሽከርካሪ እሁድ ከቀኑ 7፡15 እስከ ቀኑ 9 ሰዓት ድረስ መጓዙን ተናግረዋል። በ53 ፍርጎዎች ለቤትና መንገድ ግንባታ የሚያገለግሉ የድንጋይ ጠጠሮችን ጭኖ ሲጓዝ የነበረው ባቡሩ በሰዓት 100 ኪሎ ሜትር ፍጥነት እንደነበረውም ተነግሯል። ሆኖም በሰው ህይወት ላይ ምንም አይነት ጉዳት ሳያደርስ ባቡሩን ማስቆም እንደተቻለ ነው ሃላፊዎቹ የገለጹት። በካቱሃ ግዛት የአሽከርካሪዎችና ባለሙያዎች ቅይይር ሲደረግ ችግሩ ሊፈጠር እንደቻለ የተነገረ ሲሆን 70 ኪሎ ሜትሮችን ያለ አሽከርካሪ እንዴት ሊጓዝ ቻለ የሚለው ጉዳይ ላይ በጥብቅ ምርመራ እንደሚደረግ ቢቢሲ ዘግቧል። የቁጥጥር ባለሙያዎች ባቡሩን ለማስቆም የዛፍ ግንዶች እንደተጠቀሙ ያስነበበው ዘገባው በዚህም የባቡሩን ፍጥነት በመቀነስና በካቱሃ ግዛት እንዲቆም መደረጉን አስነብቧል።
የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም የኢትዮጵያ ድል በአፍሪካ ታሪክ ጉልህ ስፍራ እንዳለው ማሳያ ነው
Feb 17, 2024 1356
አዲስ አበባ፤ የካቲት 9/2016(ኢዜአ)፡- የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም የኢትዮጵያን ድል የሚዘክር እና ድሉ በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ አገሪቱ ያላትን ጉልህ ስፍራ የሚያሳይ መሆኑ ተገለጸ። የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን ከ128 ዓመታት በፊት በአንድነት ተሰልፈው ድል በመንሳት ነፃነታቸውን ያስከበሩበት መሆኑን ሩሲያ የዜና አገልግሎት ስፑትኒክ ዘግቧል። ስፑትኒክ የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም ምረቃን አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አማካሪ ልደት ሙለታ ጋር ቃለምልልስ አድርጓል። በዚሁ ቃለምልልስ ላይ ልደት ሙለታ ሙዚየሙ በመሀል አዲስ አበባ ላይ እንዲገነባ የተወሰነው ቦታው ለመላው ኢትዮጵያውያን ካለው ታሪካዊ ፋይዳ አንጻር መሆኑን አስረድተዋል። ሙዚየሙ የተገነባበት ቦታ ኢትዮጵያውያን ወደ አድዋ ከመዝመታቸው በፊት ከሁሉም የአገሪቱ አቅጣጫዎች በመትመም የተሰበሰቡበት መሆኑን አማካሪዋ አስገንዝበዋል። መታሰቢያ ሙዚየሙ የኢትዮጵያውያን የአንድነት ምልክት ሆኖ ከማገልገሉም በተጨማሪ የአድዋ ድል መነሻ መሆኑንም ያሳያል ብለዋል። በዚህ ታሪካዊ የአDዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም በርካታ ታሪካዊ ቅርሶች የያዘ መሆኑን ያስረዱት ልደት ሙለታ ከእነዚህ መካከል በጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ከተሰረቀበት ጣሊያን አገር እንዲመለስ የተደረገው እ.አ.አ በ1935 ኢትዮጵያውያን ከጀርመን ኢንጂነሮች ጋር በመተባበር የሰሩት የመጀመሪያ የኢትዮጵያ አውሮፕላን እንደሚገኝበት አስረድተዋል። አማካሪዋ ከአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም መገንባት ማዕከላዊ ሀሳቦች መካከል አንዱ ኢትዮጵያ በቅኝ ግዛት ወረራ ያሳየችውን ተቃውሞና አልገዛም ባይነት ለማስታወስ እና የሀገሪቱን ድል ለመዘከር ነው ብለዋል። ሁሉን አቀፍና አካታች የሆኑ ቀጠናዊና ዓለም አቀፋዊ ትብብሮችን በስፋት መጠቀም እንደሚያስፈልግ ያብራሩት አማካሪዋ ጂኦ ፖለቲካል አሰላለፎችን በመገንዘብ የታዳጊ ሀገራትን ድምጽ የሚያጎሉ ቁልፍ ዓለም አቀፍ መድረኮችን መጠቀም እንደሚገባም ጠቁመዋል። አማካሪዋ አክለውም፤ ኢትዮጵያ በቅርብ ጊዜ በብሪክስ (BRICS) ውስጥ በአባልነት መካተቷ በአለም አቀፍ ዲፕሎማሲ እና በአለም ዙሪያ ካሉ አገራት ጋር በሚደረገው የትብብር ሂደት እያደገ የመጣውን ተጽእኖ ፈጣሪነቷ ያሳያል ብለዋል።
ታንዛንያ አንድ ቢሊየን ዶላር የሚያስገኝ የካርበን ሽያጭ ፕሮጀክት ይፋ አደረገች
Feb 8, 2024 1286
አዲስ አበባ፤ ጥር 30/2016 (ኢዜአ)፦ ታንዛንያ አንድ ቢሊየን ዶላር የሚያስገኝ የካርበን ሽያጭ ፕሮጀክት ይፋ ማድረጓ ተገለጸ፡፡ ስፑትኒክ ድረገጽ የአገሪቱን ምክትል ፕሬዝደንት ቢሮ ጠቅሶ እንደዘገበው ታንዛንያ ከተጠናቀቀው የአውሮፓውያኑ 2023 ወዲህ 35 የካርበን ሽያጭ ማመልከቻዎችን ተቀብላለች፡፡ በቢሮው የአካባቢ ደህንነት ኃላፊ ሴሌማኒ ጃፎ እንደተናገሩት የካርበን ሽያጭ ለአገሪቱ የገቢ ምንጭ እየሆነ ይገኛል፡፡ የካርቦን ሽያጭ ከ2018 እስከ 2022 ባሉት አመታት በተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ የተተገበረው የካርበን ሽያጭ ለአገሪቱ ከ12 ሚሊየን ዶላር በላይ ገቢ ማስገኘቱን ተናግረዋል። “የካርቦን ሽያጭ የታንዛንያን ምጣኔ ሃብታዊ እድገት ለማገዝና የተፈጥሮ አካባቢን ለመንከባከብ የራሱ አስተዋጽኦ አለው“ ያሉት ሴሌማኒ ጃፎ ጠቀሜታውን ለህብረተሰቡ በማስረዳትና በስፋት በማሳተፍ እየተሰራበት ይገኛል ብለዋል። በዱባይ በነበረውም የኮፕ 28 የአየር ንብረት ጉዳዮች ጉባኤ ላይ የሃገራቸውን መልካም ተሞክሮ በማቅረብ ዘርፉ ላይ ከሚሰሩ አካላት አዎንታዊ ግብረመልሶች ማግኘት መቻሉን አላፊው ገልጸዋል፡፡ በተገኘው ውጤትም ታንዛንያ የአንድ ቢሊየን ዶላር የሚያስገኝ የካርበን ሽያጭ ፕሮጀክት ይፋ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ታንዛንያ ከሶስት አመታት በፊት ብሔራዊ የካርበን ሽያጭ መመሪያ በማዘጋጀት ባለድርሻ አካላት እንዲመሩበት ማድረጓ ይታወቃል፡፡ ኢትዮጵያ በደን ልማት ዘርፍ እያከናወነች ባለው ሥራ እ.ኤ.አ እስከ 2030 ከካርበን ሽያጭ 100 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ለማግኘት እቅዳ እየሰራች ይገኛል፡፡
የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና አተገባበርን የሚዳስስ ምክክር መካሄድ ጀመረ
Jan 26, 2024 1161
  አዲስ አበባ፤ ጥር 17/2016(ኢዜአ) ፦ “የአፍሪካ ብልጽግና ምክክር” በሚል መሪ ሀሳብ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና የአተገባበር ሁኔታን የሚዳስስ የመሪዎችና ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች የምክክር መድረክ በጋና እየተካሄደ ነው። ከዛሬ ጀምሮ ለሶሰት ቀናት የሚቆየው የምክክር መድረኩ የነጻ ንግድ ቀጣናው ወቅታዊ ሁኔታና የፕሮቶኮል አተገባበርን እንደሚገመግም ተመልክቷል። የጋና መንግስትና አህጉራዊ ተቋማት በጋራ ባሰናዱት የምክክር መድረክ የሀገራት መሪዎችን ጨምሮ፣ የአህጉራዊና አለማቀፋዊ ተቋማት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት እንደሚሳተፉ የጋናው ግራፊክ ኦንላየን ዘግቧል። በመድረኩ በነጻ ንግድ ቀጣናው ወቅታዊ አተገባበር የታዩ ክፍተቶችና መፍትሔያቸው እንደሚዳሰስም በመረጃው ተጠቁሟል። ጎን ለጎንም አፍሪካዊ ምርቶች ለተሳታፊዎች ቀርበው አህጉራዊ የቢዝነስ ትስስር ለመፍጠር እንደታቀደም ነው በዘገባው የተመለከተው።  
ቤጂንግ ያለ አሽከርካሪ የሚንቀሳቀሱ የፖሊስ ፓትሮሎችን አስተዋወቀች
Jan 17, 2024 546
አዲስ አበባ፤ ጥር 8/2016(ኢዜአ)፦ የቻይናዋ ቤጂንግ ከተማ ያለ አሽከርካሪ የሚንቀሳቀሱ የፖሊስ ፓትሮል ተሽከርካሪዎችን በማስተዋወቅ የእንቅስቃሴ ሙከራ አካሄደች። ተሽከርካሪዎቹ ለአካባቢ ቅኝት፣ ለህዝባዊ በአላት ደህንነት እንዲሁም ለድንገተኛ አደጋ የመከላከል ስራዎች ጥቅም ላይ እንደሚውሉ በመረጃው ተመልክቷል። ቤጂንግ እ.አ.አ በ2020 በስማርት ሲቲ ማዕቀፍ ስር 160 ስኩዌር ኪሎሜትር ስፋት ያለው አሽከርካሪ አልባ ተሽከርካሪዎች የሚንቀሳቀሱበት አካባቢ የገነባች ሲሆን የዚሁ ፕሮጀክት አካል የሆኑ አሽከርካሪ አልባ የፖሊስ ፓትሮሎችን አስተዋውቃለች። ተሽከርካሪዎቹ ደረጃ አራት ያለ አሽከርካሪ የሚያንቀሳቀስ መኪና ቴክኖሎጂ እንደተገጠመላቸው እና በየ30 ሰከንዱ ራሱን የሚያድስ ባትሪ በዚህም 100 ኪሎ ሜትር የመጓዝ አቅም እንዳላቸው ተነግሯል። በተጨማሪም ተሽከርካሪዎቹ በ120 ሜትር የአካባቢ ስፋት ውስጥ የሚካሄዱ ነገሮችን የመለየት ብቃት እና የመንገድ ደህንነት ግብረ መልስ የሚሰጥ ቴክኖሎጂ እንደተገጠመላቸው ነው የተመላከተው። በቤጂንግ አሽከርካሪ አልባ መኪኖች ልምምድ ቦታ የተዋወቁት 15 የፖሊስ ፓትሮሎች ሲሆኑ ከፖሊስ መኮንኖች ጋር በመሆን የአደጋ ጊዜ ልምምድ ማካሄዳቸውንም የዘገበው ሲጂቲኤን ነው። በአሽከርካሪ አልባ ፓትሮሎቹ የተካሄዱት ሙከራዎች በአደባባይ ዝግጅቶች ደህንነትን ማረጋገጥ፣ ህዝባዊ ማስጠንቀቂያዎችን መስጠት እና የአደጋ ጊዜ ተልዕኮዎችን መለየት መሆናቸው ተመልክቷል። በአሁኑ ወቅት በቤጂንግ አሽከርካሪ አልባ መኪኖች ልምምድ ቦታ ላይ 28 አምራች ኩባንያዎች መሰማራታቸው እና 800 ተሽከርካሪዎች ደግሞ በሙከራ ላይ መሆናቸው ተገልጿል።    
ከ 100 በላይ ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች በቻይና መንግስት የተመቻቸ የስኮላርሽፕ እድል አገኙ
Jan 15, 2024 623
አዲስ አበባ ፤ ጥር 6/2016 (ኢዜአ)፡- 143 በተለያየ የትምህርት መስክ ላይ ያሉ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በቻይና መንግስት የተመቻቸ የስኮላርሽፕ እድል አገኙ፡፡ የቻይና ኢትዮጵያ የስኮላርሽፕ ወዳጅነት ማብሰሪያ ስነስርአት ላይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሳሙኤል ክፍሌ(ዶ/ር) እንደተናገሩት የቻይና መንግስትና ዩኒቨርሲቲዎች ከአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ ጋር ጠንካራ እና ትርጉም ያለው ትብብር አላቸው ፤ፋካልቲዎችንና ተማሪዎችንም እያሰለጠኑ ነው ብለዋል፡፡ በቻይና እና በኢትዮጵያ የትምህርት አካዳሚዎች መካከል ያለው ትብብር የቻይና ኢትዮጵያ ግንኙነትን የሚያጠናክር መሆኑንም ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ዣኦ ዢዩዋን በበኩላቸው የስኮላርሽፕ እድሉ ተጠቃሚ ኢትዮጵያውያን ለሃገራቸው ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገት አስተዋፅኦ እንዲያበረክቱ ያስችላቸዋል፡፡ የአዲስ አባባ የኒቨርሲቲና ምሩቃኑ በቻይና ኢትዮጵያ ግንኙነት በጎ አስተዋፅኦ አበርክተዋል ያሉ ሲሆን በቀጣይም እንዲጠናከር አዲስ አበባ የኒቨርስቲ እንደ ድልድይ ሆኖ እንዲሰራ ጠይቀዋል፡፡ ስኮላርሽፕ ካገኙት ኢትዮጵያውያን መካከል ሙሉጌታ አየለ በሰጠው አስተያየት እድሉን ያገኘን ኢትዮጵያውያን ትምህርታችንን ለማሳደግና በሀገራችን ልማት ላይ ለመሳተፍ ያስችለናል ብሏል፡፡ የቻይና ኢትዮጵያ የስኮላርሽፕ ወዳጅነት ማብሰሪያ በተካሄደ ስነስርአት ላይ በቻይንኛ ቋንቋ ክህሎት የላቀ ውጤት ያስመዘገቡ 22 ኢትዮጵያውያን መሸለማቸውንም ፒፕልስ ዴየሊ ኦንላየን ድረገፅ ዘግቧል፡፡
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም