ቀጥታ፡
ዓለም አቀፍ ዜናዎች
የአፍሪካ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ የማግኘት የጋራ ፍላጎት ታሪካዊ ፍትህን የሚያሰፍን ነው - መሐሙድ አሊ ዩሱፍ
Jan 27, 2026 93
አዲስ አበባ፤ ጥር 19/2018(ኢዜአ):- የአፍሪካ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ አባል የመሆን የጋራ መሻት ታሪካዊ ፍትህን ማስፈንና እኩልነትን ማረጋገጥ እንደሚያስችል የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። አፍሪካ ለዘመናት ቋሚ ውክልና አለማግኘቷ የምክር ቤቱን ተአማኒነት ጥያቄ ውስጥ የሚከት ነው ሲሉም ተናግረዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ከፍተኛ ደረጃ የህዝብ የክርክር መድረክ ትላንት ማምሻውን አድርጓል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በዚሁ ወቅት በበይነ መረብ ባደረጉት ንግግር አፍሪካ የዓለም ፈተናዎች በተናጠል እንደማይፈቱ በጽኑ ታምናለች ብለዋል። ሊቀ መንበሩ ዓለም አቀፍ ህግ ከታሪክ ግንዛቤ ጋር በተሰናሰለ መልኩ መተግበር አለበት ያሉ ሲሆን በተለይም የቅኝ ግዛት እና የመዋቅራዊ ኢ-ፍትሃዊነት አሻራዎች የተለየ ትኩረት እንደሚያሻቸው አመልክተዋል። ዩሱፍ አፍሪካ ለሰላም ያላት ቁርጠኝነት ተጨባጭ መሆኑን ገልጸው በሰላም አስከባሪ አስተዋጽኦዎች፣ የጸጥታ አካላት የህይወት መስዋዕትነቶችን በመክፈል፣ ከኃይል ይልቅ ለሕጋዊ ስርዓት መስፈን በቁርጠኝነት በመስራትና የአፍሪካ ህብረት ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጋር በሰላም ጉዳይ ያለውን ጠንካራ አጋርነት በማሳያነት ገልጸዋል። አፍሪካ ለዓለም ሰላም እና ደህንነት መረጋጋጥ ብዙ ብታበረክትም አሁን በዓለም መድረክ ላይ ባላት ውክልና ላይ የኢ-ፍትሃዊነት ጉዳይ መሰረታዊ ችግር ሆኖ መቀጠሉንም ነው የተናገሩት። 55 ሀገራት እና 1 ነጥብ 4 ቢሊየን ህዝብ የያዘችው አፍሪካ 80 ዓመታትን ባስቆጠረው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታ ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ አለማግኘቷ ኢ-ፍትሃዊ ብቻ ሳይሆን የምክር ቤቱን ተአማኒነት ጥያቄ ውስጥ የሚከት ነው ብለዋል። የአፍሪካ የጋራ ፍላጎት በምክር ቤቱ ቋሚ ውክልና ከነሙሉ መብቶቿ ማግኘት ነው ያሉት ሊቀ መንበሩ ይህም እኩልነት፣ በዓለም ስርዓት ውስጥ ውጤታማነትና ታሪካዊ ፍትህ እንዲሰፍን ያደርጋል ሲሉ መግለጻቸውን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
የኢጋድ የ40 ዓመታት ጉዞ፤ ከድርቅ አደጋ ምላሽ ሰጪነት እስከ ቀጣናዊ ትስስር ተዋናይነት
Jan 21, 2026 255
በሙሴ መለሰ ምስራቅ አፍሪካ በአፍሪካ አህጉር በየጊዜው ከፍተኛ ለውጥ የሚያስተናግድ እና ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ ያለው ቀጣና ነው። ከ300 ሚሊየን በላይ ህዝብ የሚኖርበት ይህ ቀጣና ከፍተኛ የሰው ሀብት ያለው ሲሆን ፈጣን የወጣት ህዝብ እድገት እና የገበያ ተደራሽነት መስፋት እየታየበት ይገኛል። የዓለም አቀፉ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) የምስራቅ አፍሪካ አጠቃላይ ዓመታዊ ጥቅል ምርት(ጂዲፒ) እ.አ.አ በ2025 598 ነጥብ 6 ቢሊየን ዶላር መድረሱን ገልጿል። ኢትዮጵያን ጨምሮ በአፍሪካ ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት እያስመዘገቡ ያሉ ሀገራት የሚገኙበት ቀጣና ነው ምስራቅ አፍሪካ። ምስራቅ አፍሪካ ግብርና፣ ቁም እንስሳት፣ ኢነርጂ፣ ማኑፋክቸሪንግ፣ ንግድ፣ ትራንስፖርት፣ የኢኮኖሚ ኮሪደሮች እና በፍጥነት እያደገ የመጣው ዲጂታል ኢኮኖሚ እምቅ የኢኮኖሚ አቅሞቿ ናቸው። ከመልክዐ ምድራዊ አቀማመጥ አንጻርም የኢትዮጵያ ከፍታማ ስፍራዎች፣ የታላላቅ ሀይቆች ተፋሰስ እና የአፍሪካ ቀንድ ዝቅተኛ ቦታዎች ይጠቀሳሉ። ከቀይ ባህር እስከ ህንድ ውቅያኖስ ምስራቅ አፍሪካን የአፍሪካ፣ መካከለኛው ምስራቅ እና የዓለም የማሪታይም ንግድ መተላለፊያ መስመሮች ይገናኙባታል።   ይህ ስትራቴጂካዊ አቀማመጥ ምስራቅ አፍሪካ በዓለም አቀፍ ንግድ፣ ሎጂስቲክስ እና ጂኦ ፖለቲካ ውስጥ ያላትን ሚና አሳድጓል። ቀጣናው ለመረጋገት እና ለትብብር ያለው ጠቀሜታም በቀላሉ የሚታይ አይደለም። ለብዙ ክፍለ ዘመናት በምስራቅ አፍሪካ የሚገኙ የተለያዩ ማህበረሰቦች በንግድ፣ በፍልሰት እና የባህል ትስስር ተጋምደዋል። በዘመናዊው ዓለም ይህ ታሪካዊ ትስስር ለቀጣናዊ ትስስር ጠንካራ አስተዋጽኦ ያለው ነው። በሀገራት በጋራ የሚገነቡ መሰረተ ልማቶች፣ የተሳናሰኑ ፖሊሲዎች እና የሰዎችና እቃዎች ነጻ ዝውውር የኢኮኖሚ እድገት እና አጠቃላይ ልማትን የሚያሳልጥ ነው። ቀጣናዊ ትስስር የተበታተነ ገበያ ወደ አንድ ማዕቀፍ ለማምጣት፣ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግና በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ ዜጎች በተለይም ወጣቶች የስራ እድል ከመፍጠር አኳያ አስተዋጽኦወ ቁልፍ ነው። ምስራቅ አፍሪካ እንደ እድሎቹ ሁሉ በርካታ ፈተናዎች ያሉበት ቀጣና ነው። በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚፈጠረው ድርቅ እና ጎርፍ፣ ግጭት፣ መፈናቀል እና የልማት ተደራሽነት ፍትሃዊ አለመሆን በዋናነት የሚነሱ ጉዳዮች ናቸው። እነዚህ ድንበር ተሻጋሪ ፈተናዎች ከተናጠል ይልቅ የጋራ የተግባር ምላሽ ይፈልጋሉ። ፈተናዎችን ከግምት በማስገባት በቀጣናው በተደጋጋሚ ለሚከሰተው ድርቅ እና የከባቢ አየር ችግር የተቀናጀ ምላሽ መስጠት የሚያስችለው ተቋማዊ ማዕቀፍ ከ40 ዓመታት በፊት ወደ ስራ ገባ። ይህ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) ነው። የኢጋድ መቋቋም እርሾ በወቅቱ በቀጣናው ያጋጥሙ የነበሩ ቀውሶች ናቸው። እ.አ.አ በ1980ዎቹ መጀመሪያ በቀጣናው የነበረው ድርቅ እና ረሃብ የብዙ ዜጎችን ህይወት የቀጠፈ ሲሆን ይህም ቀጣናው ለአየር ንብረት ለውጥ ያለውን ተጋላጭነት በግልጽ የሚያሳይ ነው። አደጋዎቹ ድንበር ተሻጋሪ በመሆናቸው የተቀናጀ የጋራ ምላሽ የሚፈልጉ ናቸው።   ኢትዮጵያ፣ ጅቡቲ፣ ኬንያ፣ ሶማሊያ፣ ሱዳን እና ዩጋንዳ ለአንገብጋቢው ቀጣናዊ ጉዳይ ምላሽ በመስጠት ኢጋድን እ.አ.አ በ1986 አቋቋሙ። ኢጋድ በወቅቱ ሲቋቋም ዋነኛ የስራ ድርሻው የነበረው ድርቅ፣ በረሃማነት እና ሁለቱ የሚያደርሷቸውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጽእኖዎችን ለመከላከል የሚደረጉ ቀጣናዊ ጥረቶችን ማስተባበር ነው። ይሁንና የከባቢ አየር ፈተናዎቹ ከፖለቲካ አለመረጋጋት፣ ግጭት እና ካለመልማት ጋር ጥልቅ ቁርኝት ያላቸው መሆኑ አድማሱ የሰፋ ግብ ያለው ቀጣናዊ ተቋምን መፍጠር እንደሚያስፈልግ በወቅቱ ይነሳ ነበር። በዚሁ መሰረት ኢጋድ እ.አ.አ በ1996 በድጋሚ አደረጃጀቱ ተስተካክሎና የስራ ድርሻው ሰፍቶ እንደገና ተቋቋመ። ከድርቅ እና ከባቢ አየር ጉዳዮች በመሻገር ኢጋድ ሰላም እና ደህንነትን ማረጋገጥ፣ የኢኮኖሚ ትብብር እና ትስስር እንዲሁም ቀጣናዊ ትስስርን ማጎልበት የተቋሙ ቁልፍ የትኩረት መስኮች ሆነዋል። የኢጋድ ዋና መቀመጫ ጅቡቲ ነው። የሰፋው የስራ ድርሻ ኢጋድን በአፍሪካ ቀንድ የምክክር፣ የውይይት እና የተቀናጀ ልማት የጋራ ማዕቀፍ እንዲሆን አድርጎታል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) እ.አ.አ በ2026 የተመሰረተበትን 40ኛ ዓመት እንደሚያከብር ከሰሞኑ አስታውቋል። ኢጋድ በአራት አስርት ዓመታት ውስጥ በስኬት ደረጃ ሊነሱ የሚችሉ ተግባራትን አከናውኗል። ከሰላም እና ደህንነት አንጻር ኢጋድ በቀጣናው ውስብስብ የሚባሉ ግጭቶች በእርቅ እና በውይይት እንዲፈቱ አስተዋጽኦ አድርጓል። ለዓመታት በሱዳን ሲካሄድ የነበረውን የእርስ በእርስ ጦርነት እንዲያበቃ እ.አ.አ በ2005 ሁሉን አቀፍ የሰላም ስምምነት እንዲፈረም በሰላም ሂደት ውስጥ የድርሻውን ተወጥቷል። ከሰላም ስምምነቱ በኋላ ደቡብ ሱዳን በህዝበ ውሳኔ ራሷን የቻለች ሀገር ሆናለች። ኢጋድ በሶማሊያ የሰላም ጥረቶች ቁልፍ ተዋናይ ነበር። በሶማሊያ የፖለቲካ እርቅ እና መረጋጋት እንዲፈጠር ሲከናወኑ በነበሩ ስራዎች ላይ ተሳትፎ አድርጓል። ቀጣናዊ ተቋሙ ባለው የእርቅ የስራ ክፍል ግጭቶች እንዳይከሰቱና ከተከሰቱም እንዲፈቱ የበኩሉን ድርሻ እየተወጣም ይገኛል። ከተቋቋመበት የስራ ድርሻ አኳያ ኢጋድ በምግብ ደህንነት፣ በአየር ንብረት ለውጥ መከላከል እና አደጋ ስጋት አስተዳደር ላይ ሰፋፊ ተግባራትን አከናውኗል። ለአብነትም የኢጋድ የአየር ንብረት ትንበያና ትግበራ ማዕከል (ICPAC) የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓቶችን በማጠናከር፣ በአየር ትንበያዎች እና የፖሊሲ ድጋፎች አማካኝነት አባል ሀገራት ለድርቅ እና ጎርፍ አደጋዎች ምላሽ እንዲሰጡ የድርሻውን እየተወጣ ይገኛል። ይህም ቀጣናዊ የአየር ንብረት ለውጥ ምላሽን ለማጠናከርና የመንግስታትን አቅም ከመገንባት አኳያ ትልቅ ድርሻ እንደተወጣ ማዕከሉ ይገልጻል። ከኢኮኖሚ ትብብር እና ቀጣናዊ ትስስር አኳያም ኢጋድ ድንበር ተሻጋሪ ንግድ እንዲያድግ፣ መሰረተ ልማት እንዲስፋፋና ኢኮኖሚያዊ ትስስር እንዲጠናከሩ የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል። በትራንስፖርት ኮሪደሮች፣ በአርብቶ አደሮች እንቅስቃሴዎችና ቀጣናዊ ገበያዎች ላይ ኢኒሼቲቮችን በመቅረጽ በአባል ሀገራት እንዲተገበር ከማድረግ ባለፈ ድጋፉን እየሰጠ ነው። ኢጋድ በቀጣናው ለንግድ እና ለእንቅስቃሴ የሆኑ መሰናክሎች እንዲቀንሱ አስተዋጽኦ አድርጓል። ኢጋድ ከፍልሰተኞች ና ተፈናቃዮች ጋር ያሉ ችግሮች እንዲፈቱና ጉዳዩ ከፈተና ባለፈ የልማት እድል እንደሆነ በማንሳት ሁሉን አቀፍ እይታ እንዲፈጠር እየሰራ ይገኛል። በአራት አስርት ዓመታት ውስጥ ኢጋድ ተቋማዊ አቅሙን በማጠናከርና አጋርነቱን በማስፋት ረገድ የተለያዩ ስራዎችን አከናውኗል። ኢጋድ ከአፍሪካ ህብረት፣ ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት እና የአውሮፓ ህብረትን ጨምሮ ከሌሎች ዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ በትብብር እየሰራ ነው። ተቋሙ በቴክኒካዊ እና ፖለቲካዊ ደረጃዎች ለአባል ሀገራት ቋሚ የምክክር ማዕቀፍ ሆኖ እያገለገለ ሲሆን ይህም በሀገራት መካከል የጋራ መተማመንና የጋራ መግባባት እንዲኖር ያለው አስተዋጽኦ ወሳኝ የሚባል ነው። የኢጋድ የ40 ዓመታት ጉዞ በስኬቶች ብቻ የታጀበ አይደለም። ቀጣናዊ ተቋሙ ከፍተኛ ፈተናዎችም አጋጥመውታል። የመጀመሪያው በተደጋጋሚ ጊዜ የሚቀሰቀሱ እና ዘላቂ መቋጫ ያላገኙ ግጭቶችና የፖለቲካ አለመረጋጋቶች ናቸው። ጉዳዮቹ የኢጋድን የእርቀ ሰላም ጥረቶች ፈተና ውስጥ ከተውታል። አንዳንድ ጊዜ በአባል ሀገራት መካከል ያሉ መከፋፈሎች ኢጋድ ቆራጥ ውሳኔ እንዳይወስን ሲገድበው ታይቷል። የፋይናንስና ተቋማዊ አቅም ውስነነቶች የኢጋድ የተለያዩ ማዕቀፎች ትግበራ ላይ መስተጓጎሎችን ፈጥረዋል። ኢጋድ ከውጭ አጋሮች የሚያገኘው ፈንድ ከራስ ዘላቂ የፋይናንስ አቅርቦት ጋር ማመጣጠን አለመቻል የተቋሙን የዘላቂነት እና የባለቤትነት ጉዳይ ላይ ተጽእኖ አሳድረዋል። የፖለቲካ ተንታኞች ተቋሙ ከአባል ሀገራቱ የሚያገኝውን ጨምሮ ገቢ እና የፋይናንስ ቅሙን የሚያጠናክርባቸውን መንገዶች በሚገባ ማየት እንዳለበት ይመክራሉ። የአየር ንብረት ለውጥ ቀውስ ሌላኛው የኢጋድ ፈተና ነው። በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ደጋግመው የሚከሰቱ ድርቆች እና የጎርፍ አደጋዎች በተቋማዊ ምላሽና አቅም ላይ ከፍተኛ ጫና አሳድረዋል። ፈጣን የህዝብ እድገት፣ የከተሜነት መስፋፋትና መፈናቀል ጫናዎቹ ይበልጥ እንዲበረቱ አድርገዋል። ቀጣናዊ ስምምነቶችና የአሰራር ማዕቀፎችን ወደ ተጨባጭ የሀገራት ትግበራ የማሸጋገር ጉዳይም ትኩረት እንደሚያሻውም ይነሳል። የሀገራት የሚለያዩ የትኩረት መስኮች እና አቅሞች በቀጣናዊ ማዕቀፎች ሂደትና ትግበራ ላይ የራሳቸውን ተጽእኖ ያሳድራሉ። 40 ዓመታትን ያስቆጠረው ኢጋድ በምስራቅ አፍሪካ እና የአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ ትብብር ያለውን ወሳኝ ጠቀሜታ የሚያሳይ ህያው ተቋማዊ ምስክር ነው። ለድርቅ እና ረሃብ ምላሽ ከመስጠት በቀጣናዊ ሰላም፣ ደህንነት፣ አንድነት እና ልማት ቁልፍ ተዋናይነት ተሸጋግሯል። አንድነት እና የፖለቲካ ቁርጠኝነትን በኢጋድ አባል ሀገራት መካከል ማጠናከር ለቀጣናዊ የተግባር ምላሽና ለተቋሙ ዘላቂ ውጤታማነት ወሳኝ የሚባሉ ጉዳዮች ናቸው። የአባል ሀገራት የጋራ አንድነት የተረጋገጠበት ኢጋድ ለቀውሶች ምላሽ ከመስጠት ባለፈ ለጋራ ፍላጎቶች መሳካት ያለው ሚናም ያድጋል። ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም ግንባታና ዘላቂ ልማት ላይ ቀጣይነት ባለው መልኩ መዋዕለ ንዋይን ማፍሰስ የኢጋድ የትኩረት አጀንዳ ሊሆን ይገባል። የኢጋድ የሰላም እና መረጋጋት ጥረቶች በሁሉን አቀፍ አስተዳደር፣ በወጣቶችና ሴቶች የነቃ ተሳትፎ እንዲሁም በዘላቂ የሀገር ግንባታ አካሄዶች ሊደገፍ እንደሚገባ የፖለቲካ ባለሙያዎች ምክረ ሀሳባችውን ያስቀምጣሉ። የልማት ፍላጎት አለመሟላት እና የኑሮ ውድነትን ለግጭቶች አበይት መንስኤ የሆኑ ጉዳዮችን ከስር መሰረቱ መፍታት ለዘላቂ መረጋጋት ወሳኝ ነው። ኢጋድ የተጣለበትን ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ትስስር እውን የማድረግ ኃላፊነቱን የበለጠ ለመወጣት የመሰረተ ልማት ትስስሮች ማጠናከር፣ ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እውን ማድረግና በቀጣናው በፍጥነት እያደገ ለመጣው ዜጋ የስራ ፈጠራና እድሎችን የሚያሰፉ ቀጣናዊ የእሴት ሰንሰለቶችን የማስፋት ስራ ላይ አበክሮ መስራት ይኖርበታል። ፈተናዎች እንዳሉ ሆነው የኢጋድ የ40 ዓመታት ጉዞ የሚያሳየው አንድ ግልጽ ሀቅ አለ። ይህም እውነታ የምስራቅ አፍሪካ መጻኢ ጊዜ እርስ በእርስ መተሳሰርና በትብብር መቆም እንደሆነ ነው። የተቋቋመበትን አላማ ዳግም ቃል ኪዳኑን በማደስ በቁርጠኝነት መስራት ከቻለ፣ ተቋማዊ አቅሙን በሚገባ ካጎለበተ፣ በሀገራት መካከል አጋርነትና ትብብርን ካጠናከረና የዲጂታል ዘመን በሚገባ በመዋጀት ከሰራ ኢጋድ ቀጣዩ ትውልድ ሰላማዊ፣ አይበገሬናና የበለጸገ ቀጣና እንዲረከብ በማድረግ ረገድ ቁልፍ ሚና መጫወቱን መቀጠል ይችላል።
የአፍሪካ ህብረት እና ጃፓን ትብብራቸውን ለማጽናት ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ
Jan 14, 2026 238
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት እና ጃፓን በባለብዙ ወገን መድረኮች ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር እንደሚሰሩ አስታወቁ። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ከጃፓን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አያኖ ኩኒሚትሱ ጋር በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ተወያይተዋል።   የኮሚሽኑ ሊቀ መንበር የአፍሪካ ህብረት እና ጃፓን ከሶስት አስርት ዓመታት በላይ ያስቆጠረ ትብብር እንዳላቸው አውስተው በጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም (ቲካድ) ማዕቀፍ ያላቸውን ግንኙነት አንስተዋል። በዮካሃማ በነሃሔ ወር 2017 ዓ.ም የተካሄደው ዘጠነኛው የጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም(ቲካድ) በሁለቱ ወገኖች አጋርነት ውስጥ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው መሆኑን አመልክተዋል። ውይይቱ የሁለትዮሽ ትብብሩን የበለጠ ማጠናከርን ያለመ ነው። ጃፓን ለአፍሪካ የበሽታ መከላከል እና መቆጣጠር ማዕከል (African CDC) እያደረገች ያለው ድጋፍ እንዲሁም የአፍሪካ ዘላቂ እድገት እና ትስስር ለሚደግፉ የመሰረተ ልማት ስራዎች እያፈሰሰች ያለው መዋዕለ ንዋይ እያደገ መምጣቱ ተመላክቷል። የጃፓን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አያኖ ኩኒሚትሱ ዘጠነኛው የጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም (ቲካድ) በስኬት መካሄዱን አድንቀዋል። 10ኛው ቲካድ በአፍሪካ እንዲካሄድ ጃፓን ከአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ጋር በቅርበት ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗን አመልክተዋል።   ሀገራቸው የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና (AfCFTA) እና የአፍሪካ የመሠረተ ልማት ማስፋፊያ ፕሮግራም (ፒዳ) ጨምሮ የአፍሪካ ህብረት ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ቁልፍ ኢኒሼቲቮች መደገፏን እንደምትቀጥል ገልጸዋል። በሌላ በኩል ሚኒስትር ዴኤታዋ በዓለም አስተዳደር ውስጥ እያደገ የመጣውን የአፍሪካ ሚና በማንሳት የአፍሪካ ህብረት በቡድን 20 ቋሚ አባል መሆኗ ትልቅ ሽግግር መሆኑን ተነግረዋል። ባለስልጣናቱ በአፍሪካ ህብረት እና ጃፓን የከፍተኛ ደረጃ የምክክር መድረክ እና ቲካድ አማካኝነት ትብብራቸውን የበለጠ ለማጠናከር እና የባለብዙወገን ዲፕሎማሲ እንዲጸና በጋራ እንደሚሰሩ መግለጻቸውን ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የአፍሪካ ህብረት እና ጃፓን እ.አ.አ በ1993 አጋርነት መመስረታቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ። ሰላም እና ደህንነት፣ ኢኮኖሚ፣ ልማት፣ ንግድ፣ ጤና ፣ ግብርና፣ ቴክኖሎጂ እና የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ከሁለቱ ወገኖች የትብብር መስኮች መካከል ይጠቀሳሉ።
ውኃ ለአፍሪካ የኅልውና ጉዳይ ነው - መሐሙድ አሊ ዩሱፍ
Jan 12, 2026 339
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦ ውኃ ሁሉንም ዘርፍ የሚነካ አህጉራዊ የኅልውና ጉዳይ መሆኑን የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። 51ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ (PRC) መደበኛ ስብሰባ ከዛሬ ጀምሮ የሕብረቱ ዋና መቀመጫ በሆነችው አዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። ስብሰባው"ዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ደኅንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚል የአፍሪካ ሕብረት ባዘጋጀው የ2026 መሪ ሐሳብ የሚደረግ ነው።   በስብሰባው ላይ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ፣ የአፍሪካ ሕብረትና የሕብረቱ ተቋማት አመራሮች፣ የሕብረቱ አባል ሀገራት አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ተሳትፈዋል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ የዘንድሮው የአፍሪካ ሕብረት ትኩረቱን ያደረገው በውኃ ላይ መሆኑን ገልጸዋል። ውኃ በሁሉም አይነት እጅጉን ወሳኝ የሆነ ሀብት እና የኅልውና ጉዳይ መሆኑን ገልጸው፤ አህጉራዊ ግቦቹን ለማሳካት ቁልፍ ሚና እንደሚጫወት አስገንዝበዋል። በብራዚል ቤለም የተካሄደው 30ኛው የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 30) ትኩረት ከተሰጣቸው አጀንዳዎች መካከል አንዱ መሆኑንም አመልክተዋል። ኢትዮጵያ በምታዘጋጀው 32ኛው የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ 32) ውኃ አንዱ አጀንዳ እንደሚሆንም ተናግረዋል። ሊቀ መንበሩ ኢትዮጵያ ኮፕ 32ን ለማዘጋጀት በመመረጧ በድጋሚ እንኳን ደስ አላችሁ ለማለት እወዳለሁ ያሉ ሲሆን፤ ለጉባኤው ስኬታማነት ሕብረቱ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። በሌላ በኩል ሰላም እና ደኅንነት የአፍሪካ አንገብጋቢ አጀንዳ መሆኑን የገለጹት ሊቀ መንበሩ ሱዳን፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ሊቢያን በማሳያነት ጠቅሰዋል። ኢ-ሕገመንግሥታዊ ለውጦች አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሳቸውን ጠቅሰው፤ ሀገራት ዴሞክራሲያዊ ሥርዓትን እንዲያከብሩ አሳስበዋል። የአፍሪካ ሕብረት ተቋማዊ ሪፎርም እና ኢኮኖሚያዊ ትሥሥርን ጨምሮ ለአህጉራዊ አጀንዳዎች እየሠራ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። አህጉራችን ፈተናዎች ቢኖሩባትም በጋራ ከቆምን እናልፋቸዋለን ሲሉም በአጽንኦት ገልጸዋል። የዛሬው ስብስባ የካቲት 4 እና 5 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚካሄደው 48ኛው የአፍሪካ ሕብረት የሥራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ስብሰባ እንዲሁም የካቲት 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚከናወነው 39ኛው የሕብረቱ የመሪዎች ጉባኤ የሚቀርቡ ረቂቅ አጀንዳዎች ላይ ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል። 51ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ ስብሰባ እስከ ጥር 22 ቀን 2018 ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን፤ የኮሚቴው መደበኛ ስብስባ ለዋናው ጉባኤ እንደ ይፋዊ የዝግጅት ስብስባ የሚያገለግል ነው። የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ የሕብረቱን ቋሚ ተወካዮችና የአባል ሀገራቱን አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ያቀፈ መሆኑ ይታወቃል።
51ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ይጀመራል
Jan 12, 2026 351
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦ 51ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ (PRC) መደበኛ ስብሰባ ከዛሬ ጀምሮ የህብረቱ ዋና መቀመጫ በሆነችው አዲስ አበባ መካሄድ ይጀምራል። ስብሰባው "ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚል የአፍሪካ ህብረት ባዘጋጀው የ2026 መሪ ሃሳብ የሚደረግ ነው። የዘንድሮው መሪ ሀሳብ ጭብጥ በአፍሪካ የውሃ ደህንነትና ንጽህና አጠባበቅ ላይ ትኩረቱን አድርጓል። በስብሰባው ላይ የአፍሪካ ሕብረትና የሕብረቱ ተቋማት አመራሮች፣የሕብረቱ አባል አገራት አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች እንደሚሳተፉበት ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። ስብስባው የካቲት 4 እና 5 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚካሄደው 48ኛው የአፍሪካ ሕብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ስብሰባ እንዲሁም የካቲት 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚከናወነው 39ኛው የሕብረቱ የመሪዎች ጉባኤ የሚቀርቡ ረቂቅ አጀንዳዎች ላይ ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል። በተጨማሪም ኮሚቴው በአፍሪካ ሕብረት ስር የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትን የአፈጻጸም እንዲሁም ሕብረቱ እ.አ.አ በ2025 ያካሄዳቸውን ስብሰባዎች የተመለከቱ ሪፖርቶችን ያደምጣል። ሰላም እና ደህንነት፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣናን ጨምሮ የኢኮኖሚ ትስስር፣ የተቋማዊ ሪፎርሞች እና የበጀት እቅዶችን የተመለከቱ የቴክኒክ ሰነዶችንም ያዘጋጃል። ኮሚቴው በ2026 የአፍሪካ ህብረት መሪ ሀሳብ ላይ ምክረ ሀሳቦችን ያቀርባል ተብሎ ይጠበቃል። 51ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ ስብሰባ እስከ ጥር 22 ቀን 2018 ዓ.ም ይቆያል። የኮሚቴው መደበኛ ስብስባ ለዋናው ጉባኤ እንደ ይፋዊ የዝግጅት ስብስባ የሚያገለግል ነው። የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ የሕብረቱን ቋሚ ተወካዮችና የአባል አገራቱን አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ያቀፈ ነው።
የቻይና አፍሪካ ትብብር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል
Jan 8, 2026 273
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ማሕሙድ አሊ ዩሱፍ ከቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ ጋር ውይይት አካሄዱ። ውይይቱ እያደገ የመጣው የቻይና አፍሪካ ትብብርን ማጠናከር ላይ ያለመ ነው ተብሏል። ቻይና የአፍሪካ እውነተኛ አጋር መሆኗን የገለፁት የቻይና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፤ በጋራ ተጠቃሚነት ላይ ያተኮረው ፖሊሲ ጠንካራ ወዳጅነት እንዲፈጠር ማድረጉን ገልፀዋል። የቻይና አፍሪካ ግንኙነት በተለያዩ የትብብር ማዕቀፎች እያደገ መምጣቱንም ተናግረዋል። ከውይይቱ በኋላ ባወጡት የጋራ መግለጫ፤ ሁለቱ ወገኖች የዓለም ደቡባዊ ቀጣና (Global South) ሀገራትን መብትና ጥቅም ለማስከበር፣ የሉዓላዊነትን ክብር ለመጠበቅ እና ዓለም አቀፍ ግጭቶችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት በጋራ ለመሥራት መስማታቸውን አስታውቀዋል። በውይይቱ ወቅት የቻይናን የአምስት ዓመት የልማት ዕቅድ ከአፍሪካ ኅብረት የ2063 አጀንዳ ሁለተኛው የዐሥር ዓመት ትግበራ ጋር በማጣጣም ዘመናዊነትን ለማምጣት በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ ምክክር መደረጉ ተገልጿል። በዚሁ መሠረት የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጠና (AfCFTA) ስምምነቶችን ጨምሮ፣ ቻይና ያቀረበቻቸውን ዓለም አቀፍ የደኅንነትና የልማት ተነሳሽነቶች በጋራ ለመደገፍ ከስምምነት መድረሳቸውን ኢቢሲ ዘግቧል። በተጨማሪም የተፈረሙ የትብብር ስምምነቶችን በተግባር በመተርጎም እና የንግድ ልውውጥን በማሳደግ ያላቸውን ቁርጠኝነት በጋራ መግለጫቸው አረጋግጠዋል።
51ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ መደበኛ ስብሰባ በቀጣዩ ሳምንት ይጀመራል
Jan 8, 2026 238
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 30/2018(ኢዜአ)፦ 51ኛው የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ(PRC) መደበኛ ስብሰባው ከጥር 4 እስከ 22 ቀን 2018 ዓ.ም የህብረቱ ዋና መቀመጫ በሆነችው አዲስ አበባ መካሄድ ይጀምራል። ስብሰባው "ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚል የአፍሪካ ህብረት ባዘጋጀው የ2026 መሪ ሃሳብ የሚካሄድ ነው። የዘንድሮው መሪ ሀሳብ ጭብጥ በአፍሪካ የውሃ ደህንነትና ንጽህና አጠባበቅ ላይ ያተኮረ ነው። በስብሰባው የሕብረቱ ተቋማት አመራሮች፣ የሕብረቱ አባል ሀገራት አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች እንደሚሳተፉበት ኢዜአ ከህብረቱ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። ስብሰባው የካቲት 4 እና 5 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚካሄደው 48ኛው የአፍሪካ ሕብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ስብሰባ እንዲሁም የካቲት 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚከናወነው 39ኛው የሕብረቱ የመሪዎች ጉባኤ የሚቀርቡ ረቂቅ አጀንዳዎች ላይ ይወያያል ተብሎ ይጠበቃል። በተጨማሪም ኮሚቴው በአፍሪካ ሕብረት ስር የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትን የአፈጻጸም እንዲሁም ሕብረቱ እ.አ.አ በ2025 ያካሄዳቸውን ስብሰባዎች የተመለከቱ ሪፖርቶችን ያደምጣል። ሰላም እና ደህንነት፣ የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣናን ጨምሮ የኢኮኖሚ ትስስር፣ የተቋማዊ ሪፎርሞች እና የበጀት እቅዶችን የተመለከቱ የቴክኒክ ሰነዶችንም ያዘጋጃል። ኮሚቴው በ2026 የአፍሪካ ህብረት መሪ ሀሳብ ላይ ምክረ ሀሳቦችን ያቀርባል ተብሎ ይጠበቃል። የኮሚቴው መደበኛ ስብሰባ ለዋናው ጉባኤ እንደ ይፋዊ የዝግጅት ስብሰባ የሚያገለግል ነው። የአፍሪካ ሕብረት የቋሚ ተወካዮች ኮሚቴ የሕብረቱን ቋሚ ተወካዮችና የአባል ሀገራቱን አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ያቀፈ ነው።
ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓት፤ የአፍሪካ ህብረት የ2026 መሪ ሀሳብ ዋና የትኩረት አጀንዳ
Dec 26, 2025 715
39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ የካቲት 14 እና 15 ቀን 2018 ዓ.ም በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ይካሄዳል። “ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” የ2026 የአፍሪካ ህብረት መሪ ቃል ነው። መሪ ሀሳቡን ያረቀቀው የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽን ነው። የዘንድሮው መሪ ሀሳብ ጭብጥ በአፍሪካ የውሃ ደህንነትና ንጽህና አጠባበቅ ላይ ትኩረቱን አድርጓል። የዘንድሮው መሪ ቃል ከአጀንዳ 2063 ጋር የተቆራኘ መሆኑን የአፍሪካ ህብረት መረጃ ያመለክታል። ዘላቂ የውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተረጋገጠ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓት ዘላቂ ልማት፣ አካታች እድገት፣ ጤናማ ማህበረሰብና ጠንካራ ስነ ምህዳር መገንባት፣ የተፈጥሮ ሀብት ዘላቂ አጠቃቀምና የዜጎችን የኑሮ ሁኔታ ማሻሻል ከአጀንዳ 2063 ግቦች ጋር የተሳሰረ መሆኑ ተገልጿል። ሁሉም አፍሪካዊ ንጹህ፣ ደህንነቱ የተጠበቀና በቂ ውሃ ለመጠጥ፣ ለግብርና፣ ለኢንዱስትሪ እና ለሌሎች ፍላጎቶቹ እንዲያገኝ የማድረግ ራዕይን ለማስተዋወቅ እድል እንደሚፈጥርም ታምኖበታል።   ህብረቱ የውሃ ደህንነት እንደ አህጉር የተያዙ ስትራቴጂካዊ ግቦችን ለማሳካት ወሳኝ መሆኑን በማዕቀፎቹ አስቀምጧል። ውሃ እና ንጽህና የኢኮኖሚ እድሎችን በማስፋት፣ የስራ አጥነት ምጣኔን በመቀነስ፣ የስደቶችና ተፈናቃዮችን ጫና ለማቃለል እንዲሁም ለሰላምና ደህንነት መስፈን አስተዋጽኦ እንዳላቸው ተመላክቷል። የ2026 የአፍሪካ ህብረት መሪ ሀሳብ ህብረቱ ውሃ እና ንጽህና ለጤና፣ ለኢኮኖሚ እድገት፣ የምግብ ዋስትና መረጋገጥና ዘላቂ የአካባቢ ምህዳር ለመፍጠር መሰረት መሆኑን የበለጠ እውቅና እንደተሰጠው አመልክቷል። ሁሉን አቀፍ እና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይገበር የውሃ ደህንነትን የማረጋገጥ አላማ ካለው የአፍሪካ የውሃ ፖሊሲ ጋር የተጣጣመ ነው። የዘንድሮው መሪ ቃል የአፍሪካ እና ዓለም አቀፍ ጥረቶችን ያስተሳሰረ ድልድይ ሆኗል። በዘላቂ ልማት ግቦች ውስጥ ያለው ግብ ስድስት ከውሃ እና ንጽህና ጋር የተያያዘ ነው። ይህ ግብ እ.አ.አ በ2030 ለሁሌም ዜጋ ደህንነቱ የተረጋገጠ ውሃ አቅርቦትና የንጽህና አጠባበቅን ተደራሽ የማድረግ አላማ አለው። የአየር ንብረት ለውጥ፣ የህዝብ እድገት፣ የከተሜነት በፍጥነት መስፋፋትና ውሃ በአግባቡ አለመጠቀም የውሃ ደህንነት እና ዘላቂ አቅርቦት ላይ ተጽእኖ አሳድሯል። የንጽህና አጠባበቅ የአፍሪካ አንዱ ፈተና ነው። በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች መሰረታዊ የሚባል የንጽህና መጠበቂያ መሰረተ ልማቶችን አያገኙም። ይህም እንደ ኮሌራ ላሉ የውሃ ወለድ በሽታዎች መስፋፋት ምክንያት ሆኗል። የተቀናጀ የውሃ አስተዳደር ስርዓት፣ ድንበር ተሻጋሪ ትብብር፣ ለዘላቂ መሰረተ ልማት የሚፈሰወን መዋዕለ ንዋይን ማሳደግ፣ ውሃ በድጋሚ አጣርቶ መጠቀም፣ የውሃ ሀብቶችን መጠበቅ፣ ዘላቂ የውሃ ሀብት አስተዳደር እና ለውሃ ደህንነት ትኩረት የሚሰጡ ፖሊሲዎችና ማዕቀፎችን በውጤታማነት መተግበር ያሉትን እድሎች በዘላቂነት ለመፍታትና ፈተናዎችን ለመቅረፍ ያስችላል። ደህንነቱ የተረጋገጠ የፍሳሽ ማስወገጃ ስርዓት ላይ ያለፈውን ኢንቨስትመንት ማሳደግ፣ የቆሸሸ ውሃ በአግባቡ ማከም፣ የንጽህና አጠባበቅ ማስፋትና የግንዛቤ ፈጠራ ስራን በስፋት ማከናወን፣ ማህበረሰብ መር የንጽህና አጠባበቅ ኢኒሼቲቮችን ትግበራ ማስፋት፣ ጠንካራ የፖሊሲ ማዕቀፎችና ሀገር በቀል አቅምን መገንባት ደህንነቱ የተረጋገጠ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓትን መፍጠር ያስችላል። “ዘላቂ የውሃ አቅርቦት እና ደህንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ስርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” የ2026 የአፍሪካ ህብረት መሪ ቃል ለአፍሪካ ዘላቂ ልማት፣ የኢኮኖሚ እድገት እና ጤናማ ማህበረሰብ ግንባታ ያላቸውን ቁልፍ ሚና የሚያሳይ ነው። የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦትና ደህንነቱ የተረጋገጠ የንጽህና አጠባበቅን ለሁሉም ዜጎች ተደራሽ ማድረግ መሰረታዊ መብቶች እንዲጠበቁ ከማድረግ ባለፈ ለማህበረሰብ ደህንነትና የተሻለ የኑሮ ዘይቤ፣ ለአካባቢ ጥበቃና ለአፍሪካ ብልጽግና መረጋገጥ ስትራቴካዊ አቅም ናቸው። 39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ የካቲት 14 እና 15 ቀን 2018 ዓ.ም በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ በሚካሄድበት ወቅት በመሪ ሀሳቡ በጥልቀት በመምከር የተለያዩ የውሳኔ ሀሳቦች ይተላለፋል ተብሎ ይጠበቃል። ከመሪዎቹ ጉባኤ አስቀድሞ 48ኛው የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ስብሰባ የካቲት 11 እና 12 ቀን 2018 ዓ.ም እና 51ኛው የአፍሪካ ህብረት ቋሚ መልዕክተኞች ስብሰባ ከጥር 4 እስከ 22 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳሉ። ኢትዮጵያ 39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ እና የአፍሪካ ጣሊያን ስብሰባን ለማዘጋጀት ብሄራዊ የዝግጅት ኮሚቴ ተቋቁሞ እየሰራ እንደሚገኝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።
በኤርትራ መንግሥት እየደረሰብን ላለው መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብቶችና የዘር ማጥፋት ወንጀል ላቀረብነው ክስ ምላሽ እየተጠባበቀን ነው - የቀይ ባሕር አፋር ዲሞክራሲያዊ ድርጅት
Dec 24, 2025 610
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 15/2018(ኢዜአ)፦ በኤርትራ መንግሥት እየደረሰብን ላለው መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብቶችና የዘር ማጥፋት ወንጀል በተመለከተ ለአፍሪካ የሰብዓዊ እና የሕዝቦች መብቶች ኮሚሽን ላቀረብነው ክስ ምላሽ እየተጠባበቅን ነው ሲል የቀይ ባሕር አፋር ዲሞክራሲያዊ ድርጅት ገለጸ። የቀይ ባሕር አፋር ዴሞክራሲያዊ ድርጅት በኤርትራ መንግሥት አገዛዝ ደረሰብን ያለውን መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እና የዘር ማጥፋት ዘመቻ አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። ጋምቢያ(ባንጁል) የአፍሪካ የሰብዓዊ እና የሕዝቦች መብቶች ኮሚሽን የቀይ ባሕር አፋር ዴሞክራሲያዊ ድርጅት ላቀረበው ክስ የኤርትራ መንግስት ምላሽ እንዲሰጥ ክሱን መላኩን አድንቋል። በኤርትራ መንግስት ላይ የቀረቡትን ጉልህ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ክስ ተቀብሎ በመዝገብ ቁጥር 868/25 መመዝገቡን፣ የክሱ ፍሬ ነገር እና ይዘት ተቀባይነት ያለው መሆኑን እውቅና በመስጠት የኤርትራ መንግስት እንዲመልስ ክሱን መላኩን ኮሚሽኑ ማስታወቁን ገልጿል። የድርጅቱ ሊቀ-መንበር ኢብራሂም ሀሩን በመግለጫቸው እንደተናገሩት፤ የኤርትራው መንግሥት በደናክል አካባቢ በቀይ ባህር አፋር ህዝቦች እየፈፀመ ያለው መጠነ ሰፊ፣ ስልታዊ፣ መንግስታዊ መር እና ቀጣይነት ያለው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰትና የዘር ማጥፋት ወንጀል ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰ መጥቷል። በአሁኑ ወቅት እየደረሱ ነው ካሏቸው የመብት ጥሰቶች መካከልም ከህግ እና ከፍርድ ውጭ ግድያዎች እና ዘር ተኮር ጭፍጨፋ ማካሄድ፣ ያለ ፍርድ ማሰር እና ማሰቃየት፣ በሺዎች የሚቆጠሩትን መሰወር፣ የግዳጅ ወታደራዊ ምልመላ ማከናወን መሆናቸውን ለአብነት ጠቅሰው፤ በተለይም ከ300ሺህ በላይ የቀይ ባህር አፋር ህዝብን ማፈናቀል እና ፆታዊ ጥቃትን የአገዛዙ የአፈና መሳሪያ አድርጎ መጠቀሙን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ከሀገሪቱ ፖለቲካዊ አስተዳደር ማግለል፣ የቀይ ባህር አፋር ህዝብን ማንነትና ባህል ማጥፋትና ኢኮኖሚያዊ መብቶችን መጣስ ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህም ድርጅቱ የአፍሪካ የሰብዓዊ እና የህዝቦች መብቶች ኮሚሽን ከ1993 ጀምሮ በኤርትራ መንግሥት እየደረሰባቸው ያለውን የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ክስ ማቅረባቸውን ገልጸዋል። እኤአ ጁን 04 ቀን 2025 በ122 ገጽ የተደራጀ ክስ ማስገባታቸውን ጠቁመው፤ ኮሚሽኑ የኤርትራ መንግስት በ60 ቀናት ውስጥ ምላሽ እንዲሰጥ ክሱን መላኩን እንደገለጸላቸው ጠቁመዋል። ለክሱም ከተጠቀሙት ማስረጃዎች መካከል በድርጅቱ የተከናወነ የሰብዓዊ መብት ምርመራ ግኝት፣ በተባበሩት መንግስታት እና በአፍሪካ የሰብዓዊና ሕዝባዊ መብቶች በኤርትራ ላይ የተደረጉ ምርመራዎች፣ ግኝቶችና ማስረጃዎች፣ የመብት ጥሰት የደረሰባቸው የቀይ ባሕር አፋር ተጎጂ ወገኖች እንዲሁም በዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች የተገኙ የሰብዓዊ መብት ምርመራዎችን መቅረቡን ተናግረዋል። ድርጅቱ የአፋር ህዝብ ከሚደርስበት መከራ ለማዳን፣ የዓለም አቀፍ የመገናኛ ብዙሃን ድምፅ እንዲሆኑት፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ተቋማት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ የአፍሪካ ህብረት ትኩረት እንዲሰጡንና የኢሳያስ መንግስት ላይ ህጋዊ፣ ዲፕሎማሲያዊ፣ ሰብዓዊ እና ፖለቲካዊ እርምጃ እንዲወስዱ እንዲሁም ተፅዕኖ እንዲያሳድሩ ለማድረግ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል።
የአፍሪካ ህብረት እና አሜሪካ ጸንቶ የቆየ አጋርነት አላቸው-ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ
Dec 23, 2025 510
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 14/2018 (ኢዜአ)፦የአፍሪካ ህብረት እና አሜሪካ በጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ እና ለረጅም ጊዜ ፀንቶ የቆየ አጋርነት አላቸው ሲሉ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ገለጹ። በአሜሪካ የአፍሪካ ህብረት ልዑክ ኃላፊ አምባሳደር ኮንስታንሲያ አዴሊና ጋስፓራስ የሹመት ደብዳቤያቸውን ለአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አቅርበዋል። ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በነጩ ቤተ መንግስት (ዋይት ሃውስ) በተካሄደ ስነ ስርዓት የአምባሳደር ኮንስታንሲያን ሹመት በይፋ ተቀብለዋል። አምባሳደሯ በዋሺንግተን ዲሲ በሚገኘው በአሜሪካ የአፍሪካ ህብረት ልዑክ ቢሮ ስራቸውን በይፋ ጀምረዋል። ዶናልድ ትራምፕ የአምባሳደር ኮንስታንሲያ የልዑኩ መሪ ሆኖ መመረጥ በጋራ የኢኮኖሚ እድሎች፣ በሉዓላዊ አመራር ሰጪነት እንዲሁም በሰላም እና ደህንነት ላይ የተመሰረተውን የአፍሪካ ህብረት እና አሜሪካ ጽኑ አጋርነት የሚያንጸባርቅ ነው ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት እና አሜሪካ ላለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ገደማ በአፍሪካ ሰላም፣ ብልጽግና እና መረጋጋትን ማረጋገጥን ዋና ማዕከል ያደረገ ጠንካራ የአጋርነት ስራ እያከናወኑ እንደሚገኝ የህብረቱ መረጃ ያመለክታል።
ኬንያ ከኢትዮጵያ ጋር በቀጣናው ሰላም እና መረጋጋት ያላትን አጋርነት የማጠናከር ፍላጎት አላት -ተሰናባቹ የኬንያ አምባሳደር ጆርጅ ኦሪና
Dec 20, 2025 541
አዲስ አበባ፤ ታህሳስ 11/2018 (ኢዜአ)፦ ኬንያ ከኢትዮጵያ ጋር ሽብርተኝነትን መዋጋትን ጨምሮ በቀጣናዊ ሰላም እና መረጋጋት ያላትን አጋርነት ለማጎልበት በጋራ መስራቷን እንደምትቀጥል ተሰናባቹ በኢትዮጵያ የኬንያ አምባሳደር ጆርጅ ኦሪና ገለጹ። አምባሳደር ጆርጅ ኦሪና የኢትዮጵያ እና ኬንያ የሁለትዮሽ ትብብር ጥልቅ የታሪክ ትስስር ያለው መሆኑን ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ገልጸዋል። ሀገራቱ የኬንያው የመጀመሪያ ፕሬዝዳንት እና መስራች አባት ጆሞ ኬንያታ እና ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ጊዜ አንስቶ ወዳጅነት እንደነበራቸው አውስተው ትብብሩ በከፍተኛ ደረጃ በሚደረጉ ጉብኝቶች እና ውይይቶች እየተጠናከረ መምጣቱን አመልክተዋል። በአፍሪካ ቀንድ ሰላም እና መረጋጋት እንዲሰፍን ጠንካራ አጋርነት ፈጥረው እየሰሩ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በሶማሊያ በአፍሪካ ህብረት ሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች ጨምሮ በቀጣናው ሽብርተኝነትን በመዋጋት እና ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ በሚደረጉ ጥረቶች ላይ በትብብር እየሰሩ እንደሚገኙ አመልክተዋል። ሰላም እና ደህንነት ለቀጣናው ዘላቂ ልማት ጠንካራ መሰረቶች ናቸው ብለዋል። በሌላ በኩል የኢትዮጵያ እና የኬንያ የንግድ ትብብር እያደገ መምጣቱን የገለጹት ተሰናባቹ አምባሳደር የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና የሀገራቱን የኢኮኖሚ ትብብሩን አድማስ የበለጠ እንደሚያሰፋው ነው የተናገሩት። ቱሪዝም እና ንግድ የህዝብ ለህዝብ ትስስር እንዲጎለብት ጉልህ ድርሻ እየተወጣ ነው ብለዋል። በቀጣይም የሁለቱ ሀገራት ቀጣናዊ ትስስር እንዲጎለብት በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል። ኢትዮጵያ፣ ኬንያንና ደቡብ ሱዳንን በትራንስፖርት የሚያስተሳስረው የ"ላፕሴት ፕሮጀክት" እና የምስራቅ አፍሪካ የኃይል ቋት ጨምሮ በሌሎች መሰረት ልማት ፕሮጀክቶች ቀጣናዊ ትስስሩን የሚያሳልጡ ትልቅ አቅም መሆናቸውን ተናግረዋል። አምባሳደር ጆርጅ ኢትዮጵያ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በማስመረቋ እንኳን ደስ አላችሁ ያሉ ሲሆን ግድቡ በቀጣናው ሽግግርን የሚፈጥር ግዙፍ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እና ኬንያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እ.አ.አ በ1963 መሆኑን መረጃዎች ያመለክታሉ። ቀጣናዊ መረጋጋት እና ደህንነት ፣ ንግድ እና የመሰረት ልማት ትስስር የሀገራቱ ዋንጫ የትብብር መስኮች ናቸው።
ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ስለ ህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ የኢትዮጵያ ጉብኝት ምን አሉ?
Dec 17, 2025 552
የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ በኢትዮጵያ ይፋዊ የስራ ጉብኝት አድርገዋል። ሞዲ በኢትዮጵያ ጉብኝት ሲያደርጉ የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ከማንሞሃን ሲንግ በኋላ ኢትዮጵያን የጎበኙ ሁለተኛው ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዋል። የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት ህንድ ኢትዮጵያን ጨምሮ ከአፍሪካ ጋር ያላትን የልማት አጋርነት ማሳደግን ያለመ ነው። የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ በኢትዮጵያ ቆይታቸው ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ላይ መክረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አባላት በፓርላማ ተገኝተው ንግግር አድርገዋል። በአድዋ ድል መታሰቢያም የአበባ ጉንጉን አኑረዋል። ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ስለ ህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ የኢትዮጵያ ጉብኝት በስፋት ዘግበውታል። ዓለም አቀፍ የዜና ወኪሎቹ ሮይተርስ እና አሶሲዬትድ ፕሬስ ጉብኝቱን ከ"ጂኦ-ፖለቲካዊ" አንጻር ተመልክተውታል። በተለይ ህንድ በኢትዮጵያ ያላትን የአምስት ቢሊዮን ኢንቨስትመንት አጉልተዋል። አልጀዚራ ትኩረቱን ያደረገው ህንድ በ"ደቡባዊው ዓለም" (Global South) ላይ ያላትን ተጽዕኖ ለማሳደግ በምታደርገው ጥረት ላይ ነው። እንዲሁም የኢትዮጵያና የህንድ ስትራቴጂካዊ አጋርነት በመካከለኛው ምስራቅና በአፍሪካ ቀንድ ያለውን ዲፕሎማሲያዊ ፋይዳም በስፋት አንስቷል። ቢቢሲ እና ፍራንስ 24 ደግሞ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለየት ያለ አቀባበል ትልቅ የዲፕሎማሲያዊ መቀራረብ ምልክት መሆኑን ዘግበውታል። የአፍሪካ ሚዲያዎች በበኩላቸው የናሬንድራ ሞዲን ጉብኝት "የአፍሪካ-ህንድ" ግንኙነት አዲስ ምዕራፍ አድርገው ዘግበዋል። አፍሪካ ኒውስ እና ዘ ኢስት አፍሪካን ጉብኝቱ በአፍሪካ ህብረት ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ መደረጉን በማንሳት፣ ህንድ ከአህጉሪቱ ጋር ያላትን ወታደራዊ፣ የጤና እና የቴክኖሎጂ ትብብር እንደሚያጠናክረውም ገልጸዋል። የደቡብ አፍሪካው ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን፣ የናይጄሪያ እና ሌሎች የአፍሪካ መገናኛ ብዙሃን ህንድ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ግንኙነት ለማጠናከር ኢትዮጵያን እንደ መግቢያ በር (Anchor) መጠቀሟን እና ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት የሚኖረውን ተምሳሌትነት ዘግበዋል። እንደ ታይምስ ኦፍ ኢንዲያ (The Times of India) ፣ ኤንዲቲቪ (NDTV) እና ኤኤንአይ (ANI) ያሉ የህንድ መገናኛ ብዙሃን የሞዲን ጉብኝት ከፍተኛ ሽፋን ሰጥተውታል። የዘገባዎቹ ዋንኛ ትኩረት በኢትዮጵያ ፓርላማ ስላደረጉት ንግግር እና ስለተደረገላቸው ልዩ የክብር ሽልማት ነው። በሌላ በኩልም የዲጂታልና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የተደረጉ ስምምነቶችን በዝርዝር አቅርበዋል። አጠቃላይ የመገናኛ ብዙሃን ዘገባዎች ትኩረት ታሪክ፣ ስትራቴጂካዊ አጋርነት፣ የደቡብ ለደቡብ ትብብር ላይ ያጠነጠኑ ናቸው። የኢትዮጵያ እና ህንድ የሁለትዮሽ ትብብር ወደ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ምዕራፍ መሸጋገሩንም በመገናኛ ብዙሃኑ በስፋት ተነስቷል። ኢትዮጵያ እና ህንድ የተባበሩት መንግስታ ድርጅት እና ብሪክስን ጨምሮ በሌሎች የባለብዙወገን መድረኮች ላይ የደቡባዊውን ዓለም ድምፅ ለማሰማት የጋራ ቁርጠኝነታቸውን መግለጻቸው በዘገባዎቹ በስፋት ተንጸባርቋል።  
የመጀመሪያው የአፍሪካ ሚዲያ ሽልማት ዛሬ በአዲስ አበባ ተካሂዷል
Dec 4, 2025 917
አዲስ አበባ፤ ህዳር 25/2018(ኢዜአ)፦ የመጀመሪያው የአፍሪካ ሚዲያ ሽልማት ዛሬ ማምሻውን በአዲስ አበባ ተከናውኗል።   በዕውቅና መርሃ ገብሩ የኢፌዴሪ መንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር እናትአለም መለሰ እንዲሁም ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች፣ የተለያዩ ሀገራት የኮሙኒኬሽንና ኢንፎርሜሽን ዘርፍ ሚኒስትሮችና ተወካዮች እንዲሁም የሚዲያ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ሽልማቱ ለአፍሪካ ጋዜጠኝነት፣ ብሮድካስት ሚዲያ፣ ዲጂታል ሚዲያ እና ዘገባዎች እውቅና የሰጠ ነው። በአፍሪካ ሚዲያ ምህዳርን በመቅረጽ ሚናቸውን የተወጡ ጋዜጠኞች ተሸልመዋል። ምርጥ የዜና ዘገባ፣ ምርጥ ቃለ መጠይቅ፣ ምርጥ ዶክመንተሪ፣ ምርጥ ወቅታዊ ፕሮግራም፣ ምርጥ አፍሪካ ተኮር የመዝናኛ ፕሮግራምና ምርጥ የቪዲዮ ፕሮዳክሽን በመገናኛ ብዙሃን ዘርፍ እና ሽልማት የተሰጠባቸው ዘርፎች ናቸው።   አፍሪካ ተኮር ምርጥ የማህበራዊ ሚዲያ ተንቀሳቃሽ ምስል፣ ምርጥ የወቅታዊ ጉዳይ የማህበራዊ ሚዲያ ተንቀሳቃሽ እና ምርጥ አጭር የማህበራዊ ሚዲያ ተንቀሳቃሽ ምስል የማህበራዊ ሚዲያ ሽልማት የተሰጠባቸው ዘርፎች ናቸው። ሁሉም እጩዎች 2000 ዶላር ሽልማት ያገኙ ሲሆን በእያንዳንዱ ዘርፍ ያሸነፉ ተወዳዳሪዎች የስድስት ሺህ ዶላር ሽልማት አግኝተዋል። የምርጦች ምርጥ የይዘት ፈጣሪዎች አሸናፊም "The Golden Alkebulan" የተሰኘ ልዩ በወርቅ የተለበጠ የዋንጫ ተሸላሚ ሆኗል። በሽልማቱ ላይ ከ40 ሀገራት በላይ የተወጣጡ የሚዲያ ባለሙያዎች ከ800 በላይ ስራዎችን ማቅረባቸውን ተገልጿል። የአፍሪካ ሕብረት ብሮድካስቲንግ፣ የፓትሪስ ሉሙምባ ፋውንዴሽን፣ የክዋሜ ንክሩማህ ፋውንዴሽን፣ የምዋሊሙ ኒዬሬሬ ፋውንዴሽን፣ የኬኔት ካውንዳ ሌጋሲ ፋውንዴሽን፣ የሲሱሉ ፋውንዴሽን ለማኅበራዊ ፍትህ፣ የፒኤልኦ ሉሙምባ ፋውንዴሽንና የሩስያው አር ቲ ሚዲያ የሽልማቱ አጋር ናቸው።
ግድቡ አፍሪካውያን ለጋራ ራዕይ ከቆሙ ህልማቸውን ማሳካት እንደሚችሉ ያሳየ ነው - የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት አሸናፊዎች እና ተሳታፊ ጋዜጠኞች
Dec 1, 2025 792
አዲስ አበባ፤ ህዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አፍሪካውያን ለጋራ ራዕይ ከቆሙ ህልማቸውን ማሳካት እንደሚችሉ ያሳየ ነው ሲሉየምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የሚዲያ ሽልማት አሸናፊዎች እና ተሳታፊ ጋዜጠኞች ገለጹ። የታላቁ ሕዳሴ ግድብ የአፍሪካን ትርክት በመቀየር ትልቅ ሚና የሚወጣ ግዙፍ ፕሮጀክት መሆኑንም ተናግረዋል። ሶስተኛው የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት ለሁለት ቀናት በአዲስ አበባ ኢትዮጵያ መካሄዱ ይታወቃል። የሶስተኛው የኢጋድ የሚዲያ ሽልማት አሸናፊዎች እና ተሳታፊ ጋዜጠኞች ዛሬ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን ጎብኝተዋል። በሴት ጋዜጠኞች ዘርፍ አሸናፊ ከሆኑት መካከል ዩጋንዳዊቷ ጋዜጠኛ አይባሬ ሲንደሬላ ኢትዮጵያ በዜጎቿ አስተዋጽኦ ህዳሴ ግድብን ለመገንባት ያሳየችውን ቁርጠኝነት አድንቃለች። በበርካታ ሀገራት ዜጎች ከሚከፍሉት ታክስ ተጨባጭ ውጤቶችን እምብዛም ሲያዩ አይስተዋልም ያለችው ጋዜጠኛዋ ኢትዮጵያ በግልጽነትና በጠንካራ ራዕይ የህዝብን ሀብቶች አሻጋሪ ብሄራዊ ፕሮጀክት መቀየሯን ተናግራለች። የአፍሪካ መሪዎች ከሕዳሴ ግድብ ጠቃሚ ተሞክሮዎችን ሊወስዱ ይገባል ብላለች። የኬንያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ከፍተኛ አዘጋጅ አሻ ሃሚሲ አፍሪካውያን የራሳቸውን ችግሮች ያለ ምንም ጣልቃ ገብነት መፍታት እንዳለባቸው ገልጻለች። ሕዳሴ ግድብ ዜጎች ለሀገራቸው መስዋዕትነት እንደሚከፍሉ የሚያሳይ ፕሮጀክት ነው ያለችው አሻ ይህም በህዝብ እና በመንግስት መካከል ያለ መተማመንና ነገን የተሻለ ለማድረግ ዛሬ ላይ መስራት ያለውን ቁርጠኝነት የሚያመላከት ነው ብላለች። ግድቡ አፍሪካውያን ለጋራ ራዕይ ከቆሙ ህልማቸውን ማሳካት እንደሚችሉ ያሳየ እንደሆነም ተናግራለች። በኢጋድ ሚዲያ ሽልማት በዲጂታል ሚዲያ ዘርፍ ካሸነፉት ጋዜጠኞች መካከል አንዱ የሆነው ደቡብ ሱዳናዊው የፊልም ባለሙያ እና ተራኪ ጋብርኤል ጋትሉዋክ ዋል ኬት በበኩሉ ህዳሴ ግድብ አፍሪካ ያላትን አቅም በተግባር ያሳየ ነው ሲል ተናግሯል። ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን የመሰለ ግዙፍ ፕሮጀክት ካሳካች ሌሎች ሀገራትም ይህን ፈለግ ተከትለው ትላልቅ ፕሮጀክቶችን እውን ማድረግ ይችላሉ ብሏል። አፍሪካውያን ሀገራቸውን በራሳቸው መገንባት እንደሚችሉ ማመን አለባቸው ያለው ኬት የራሳቸውን ዕጣ ፈንታ ሌሎች እንዲወስኑላቸው መፍቀድ የለባቸውም ሲልም ገልጿል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነቢያት ጌታቸው ለሕዳሴ ግድብ ኢትዮጵያን እና በውጭ የሚኖሩ ዳያስፖራዎች የከፈሉትን መስዋዕትነት አንስተዋል። ሕዳሴ ግድ የአፍሪካ የስኬት ተምሳሌት ፕሮጀክት እንደሆነ ገልጸው ከግድቡ የሚገኘው የኤሌክትሪክ ኃይል ጎረቤት ሀገራትን ተጠቃሚ እንደሚያደርግ አመልክተዋል። ይህም ቀጣናዊ ትስስርን የሚያጠናክርና የአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ራዕይ የሆነውን የበለጸገች እና የተሳሰረች አፍሪካን የመፍጠር ራዕይን እንደሚደግፍም ተናግረዋል። ግድቡ የአፍሪካን ትርክት የመቀየር ትልቅ ኃይል ያለው ፕሮጀክት ነው ብለዋል አምባሳደሩ።
የአፍሪካን ዘላቂ የልማት ግቦች ለማሳካት ዓለም አቀፍ ትብብርን በማጠናከር በቁርጠኝነት መስራት ያስፈልጋል
Nov 21, 2025 1030
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 12/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካን ዘላቂ የልማት ግቦች ለማሳካት በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ዓለም አቀፍ ትብብርን በማጠናከር በቁርጠኝነት መስራት እንደሚያስፈልግ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ገለጸ። በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን አዘጋጅነት የ2025 የአፍሪካ ዘላቂ የልማት ሪፖርት ዋና ዋና ግኝቶችና የፖሊሲ ምክረ ሃሳቦች ላይ የዌብናር ውይይት ተካሂዷል። በመድረኩም የአፍሪካ ሕብረት አባል ሀገራት ወሳኔ ሰጪዎች፣ ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ማህበረሰቦች፣ ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ የገንዘብ ተቋማት፣ ተመራማሪዎችና የልማት አጋሮች ተሳትፈዋል። በመንግስታቱ ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን የልማት ዕቅድ ክፍል ኃላፊ ኦዬባንኬ አበጂሪን፤ የምንፈልጋትን አፍሪካ ዕውን ለማድረግ በዘላቂ የልማት ግቦች ላይ በትብብር መስራት ያስፈልጋል ብለዋል። የአፍሪካ ሀገራት የ2030 ዘላቂ የልማት አጀንዳና የአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 አፈፃጸም ሂደትን የሚከታተል የሪፖርት ሥርዓት መኖሩንም ገልጸዋል። እ.ኤ.አ በ2017 የተጀመረው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ሪፖርት ክትትል ሥርዓትም የአህጉሪቷን ዘላቂና ቁልፍ የልማት ማዕቀፎች አፈፃጸም የሚገመገምበትን መድረክ በማመቻቸት ወሳኝ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ተናግረዋል። እ.ኤ.አ የ2025 የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ሪፖርት መድረክም የአህጉሪቷ ልማት በሳይንስና ማስረጃ የተመሰረቱ የመፍትሔ አፈፃጸሞችን ያመላከተ መሆኑን አስገንዝበዋል። ሪፖርቱም የአፍሪካ ዕድገት በጤና፣ በሥርዓተ ፆታ እኩልነት፣ በኢኮኖሚ ዕድገት፣ በውቅያኖስ ጥበቃና ዓለም አቀፍ ሽርክና ጋር በአፍሪካ ሀገራት እ.ኤ.አ የ2030 ዘላቂ የልማት ግብና የአፍሪካ ሕብረት አጀንዳ 2063 ወሳኝ አካል መሆኑን አስረድተዋል። የአህጉሪቷን ዘላቂ የልማት ግቦች ለማሳካትም በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ የትብብር ሥርዓትን በማጠናከር በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የ2025 የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ሪፖርትም ወሳኝ የአፈፃጸም ግኝቶችን በማረም የፖሊሲ ምክረ ሃሳቦችን በሚገባ ለመተግበር አቅም እንደሚፈጥር አስረድተዋል። በመድረኩም የአህጉሪቷን ዘላቂ የልማት ግቦችና አጀንዳዎች የአፈፃጸም ስኬት ልምድና ተሞክሮ በመለዋወጥ የፖሊሲ አቅጣጫዎችን ለመቅረጽ የሚችል ተግባቦት መፈጠሩን አስገንዝበዋል። በቀጣይም የአህጉሪቷን የልማት ግቦች ለማሳካትም አዲስ ዓለም የፋይናንስ ድጋፍ ማዕቀፍ አስፈላጊነትን ታሳቢ በማድረግ በትኩረት የሚሰራበት ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። መድረኩም ብሔራዊና ቀጣናዊ የልማት ስኬት አፈፃጸም የአሰራር ስርዓቶችን በመፈተሽ ዕድሎችን በማስፋት የአህጉሪቷን ዘላቂ የልማት አጀንዳዎ ማሳካት እንደሚያስፈልግም አጽንኦት ሰጥተዋል።
የአፍሪካ ህብረት እና ማሌዥያ የአጋርነት አድማሳቸውን ለማስፋት እንደሚሰሩ ገለጹ
Nov 20, 2025 879
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 11/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት እና ማሌዥያ በትምህርት እና ዲጂታል ዘርፍ ጨምሮ በተለያዩ መስኮች ያላቸውን አጋርነት ለማጠናከር በቅርበት እንደሚሰሩ አስታወቁ። የማሌዥያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዳቶ ሰሪ አንዋር ቢን ኢብራሂም በአፍሪካ ህብረት ዋና ኮሚሽን ዛሬ ይፋዊ የስራ ጉብኝት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ህብረቱን የጎበኙ የመጀመሪያ ማሌዥያ መሪ ሆነዋል።   የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ከማሌዥያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዳቶ ሰሪ አንዋር ቢን ኢብራሂም ጋር ተወያይተዋል። ውይይቱ ሁለቱ ወገኖች በተለያዩ መስኮች ያላቸውን አጋርነት ማጠናከርን ያለመ ነው። ሊቀመንበሩ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጉብኝት የአፍሪካ እና ማሌዥያ ትብበር ውስጥ ታሪካዊና የሁለቱን ወገኖች ስትራቴጂካዊ ትብብር እንደሚያጠናክር አመልክተዋል። እ.አ.አ በ2024 የአፍሪካ እና ማሌዥያ የንግድ ልውወጥ መጠን 7 ነጥብ 5 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር መድረሱን ጠቅሰው፤ ይህም በዘርፉ ያለው ትብብር እየተጠናከረ መምጣቱን የሚያሳይ ነው ብለዋል። ትምህርት የሁለቱ ወገኖች አጋርነት ዋነኛ ምሰሶ መሆኑንና ከእ.አ.አ 2012 አንስቶ ከ40 ሺህ በላይ አፍሪካውያን በማሌዥያ ትምህርታቸውን መከታተላቸውን ገልጸዋል።   ማሌዥያ ቀጣይ የደቡብ ምስራቅ እስያ ሀገራት ሊቀ መንበር መሆኗ እና ብሪክስን ለመቀላቀል ያላት ፍላጎት ኢንቨስትመንትን ጨምሮ ከአፍሪካ ጋር ያለውን ትብብር ለማጠናከር መልካም አጋጣሚ ይፈጥራል ነው ያሉት። ሁለቱ ወገኖች በዲጂታል ኢኖቬሽን፣ በግብርና ማቀነባበሪያ ልማት፣ በደቡብ ደቡብ ንግድ እና ትምህርት ዘርፍ ያላቸውን አጋርነት ለማጠናከር ያላቸውን የጋራ ቁርጠኝነት ገልጸዋል። ሊቀ መንበሩ የአፍሪካ ህብረት እና ማሌዥያ ዓመታዊ ምክክር እ.አ.አ በ2026 እንዲካሄድ ሀሳብ አቅርበዋል። የማሌዥያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዳቶ ሰሪ አንዋር ቢን ኢብራሂም በበኩላቸው፤ ማሌዥያ እና አፍሪካ ንግድ፣ ግብርና እና ትምህርትን ጨምሮ በቁልፍ ጉዳዮች ትብብር እያደገ መምጣታቸውን አመልክተዋል።   ሁለቱ ወገኖች ያላቸውን የትብብር አድማስ በማስፋት የጋራ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ መስራት እንደሚገባቸው መግለጻቸውን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። በውይይቱ ላይ የማሌዥያ መንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት ተሳትፈዋል። የአፍሪካ ህብረት እና ማሌዥያ የአጋርነታቸውን አድማስ ለማስፋት እንደሚሰሩ ገልጸዋል::
ለሱዳን ግጭት ዓለም አቀፍ የተቀናጀ የተግባር ምላሽ ያስፈልጋል- ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)
Nov 19, 2025 754
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 10/2018(ኢዜአ)፦ የሱዳን ግጭት ዘላቂ መፍትሄ እንዲያገኝ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የተቀናጀ ምላሽ እንዲሰጥ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ጥሪ አቀረቡ። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ያዘጋጀው ሁለተኛ የሱዳን የልዩ ልዑኮች ፎረም ዛሬ በጅቡቲ ተካሄዷል። በፎረሙ ላይ የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)፣ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፍ ተዋንያን ተሳትፈዋል። ፎረሙ በሱዳን ላለው ቀውስ የተቀናጀ መልስ መስጠት በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ያተኮረ ነው።   የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) በፎረሙ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር የሱዳን ሰላም በሱዳናውያን የሚመራ፣ ቀጣናዊ ትብብር የተረጋገጠበት እና ዓለም በአንድ ድምጽ የሚደግፈው ሊሆን እንደሚገባ አመልክተዋል። በሱዳን ያለውን ግጭት ለማስቆም፣ ንጹሃን ዜጎችን ለመጠበቅ እና የኢጋድ ቀጣናን የተረጋጋ ለማድረግ በቅንጅት መስራት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ዋና ፀሐፊው ኢጋድ ከአፍሪካ ህብረት እና ዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በመሆን በሱዳን የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ እንዲደረስ፣ የሰብዓዊ እርዳታ መተላለፊያ እንዲከፈት እና ተአማኒነት ያለው የስልጣን ሽግግር እንዲኖር በቁርጠኝነት ይሰራል ብለዋል። ኢጋድ ሱዳናውያን በሀገራቸው ሰላም እና ደህንነት እንዲረጋገጥ እንዲሁም ክብራቸው እንዲጠበቅ ያላቸው መሻት እንዲሳካ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ በመረጃው አመልክቷል።
የአፍሪካ መሪዎች ብዝሃ ህይወትን ከብሄራዊ ፖሊሲዎቻቸው ጋር ማስተሳሰር ይገባቸዋል -አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ
Nov 6, 2025 999
አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 27/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ መሪዎች የብዝሃ ህይወት አጀንዳን ከብሄራዊ ፖሊሲዎቻቸው ጋር በማቆራኘት ሊተገብሩ እንደሚገባ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ ገለጹ። ከጥቅምት 23 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በቦትስዋና ጋቦሮኒ ሲካሄድ የቆየው የመጀመሪያው የአፍሪካ የብዝሃ ህይወት ጉባኤ በመሪዎች ደረጃ በተደረገ ስብስባ ተጠናቋል። በጉባኤው ላይ የሀገራት መሪዎች፣ የአካባቢ ጥበቃ ሚኒስትሮች፣ የዓለም የብዝሃ ህይወት ጥበቃ መሪዎች እና ተመራማሪዎች፣ ሀገር በቀል የማህበረሰብ መሪዎች፣ ባለሀብቶች፣ የግሉ ዘርፍ ተዋንያን፣ የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት፣ ዓለም አቀፍ አጋሮች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳታፊ ሆነዋል። “የብዝሃ ህይወትን በዘላቂነት በመጠቀም የአፍሪካን ብልጽግና ማረጋገጥ” የጉባኤው መሪ ሀሳብ ነው። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር አምባሳደር ሳልማ ማሊካ ሃዳዲ ጉባኤው አፍሪካ የተፈጥሮ ሀብቷን ለመጠበቅ በጀመረችው ጉዞ ውስጥ ታሪካዊ ሁነት መሆኑን ገልጸዋል። ከኮንጎ ጥብቅ ደን እስከ ደቡብ አፍሪካው የኬፕ የአበባ ሀብት ቀጣና በአህጉሪቷ የሚገኙ ተፈጥሯዊ ምህዳሮች የህይወት፣ ባህል እና የኢኮኖሚ እድገት ምንጮች መሆናቸውን አመልክተዋል።   የአየር ንብረት ለውጥ፣ ብክለት እና ዘላቂ ያልሆነ የተፈጥሮ ሀብት አጠቃቀም በአፍሪካ የብዝሃ ህይወት ላይ ስጋቶችን እንደደቀኑ ተናግረዋል። የብዝሃ ህይወት ጥበቃ ላይ የተቀናጀ የተግባር ምላሽ ያስፈልጋል ያሉት አምባሳደሯ ለዘርፉ የሚያስፈልገውን መዋዕለ ንዋይ ማፍሰስ ይገባል ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ከአባል ሀገራት፣ ከቀጣናዊ ተቋማት፣ ሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት እና የግሉ ዘርፍ ጋር በመሆን የአፍሪካ ብዝሃ ህይወት ስትራቴጂ ከአጀንዳ 2063 እና ከተባበሩት መንግስታት ድርጅት የዘላቂ ልማት ግቦች ጋር በተጣጠመ መልኩ እንዲተገበር በትብብር እንደሚሰራ ነው የገለጹት። ብዝሃ ህይወት እንደ ተጓዳኝ ጉዳይ ሳይሆን ለአፍሪካ ሰላም፣ አይበገሬነት እና ዘላቂ ልማት ባለው ቁልፍ ድርሻ ሊታይ እንደሚገባ ጠቅሰው በዚህ ረገድም የአፍሪካ መሪዎች ብዝሃ ህይወት ከብሄራዊ ፖሊሲዎች ጋር ማስተሳሰር እንዳለባቸው አሳስበዋል። ወጣቶች እና ሀገር በቀል ማህበረሰቦችን ማብቃት እንዲሁ በፋይናንስ እና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዓለም አቀፍ እኩልነት ለማስፈን መትጋት ትኩረት እንደሚያሻቸው ነው ያነሱት። የአፍሪካ ብልፅግና አረንጓዴ፣ ሁሉን አቀፍ እና ተፈጥሮን መሰረት ያደረገ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። የጋቦሮኒው ጉባኤ የአፍሪካ ብዝሃ ህይወት ድንጋጌ ቀጣይ ለሚመጡ ትውልዶች መሰረት የሚጥል እንደሚሆንም ገልጸዋል። ጉባኤው በአፍሪካ ብዝሃ ህይወት ሀብቶች፣ እድሎች፣ ፈተናዎችና ቀጣይ እርምጃዎች በዋናነት መምከሩን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
በሄይቲ እና ጃማይካ ከባድ አውሎ ነፋስ ባስከተለው ጎርፍ ሳቢያ የበርካቶች ሕይዎት አለፈ
Oct 31, 2025 955
አዲስ አበባ፤ጥቅምት 21/2018 (ኢዜአ)፡-በሄይቲ እና ጃማይካ የተከሰተው ‘ሃሪኬን ሜሊሳ’ የተሰኘው ወጀብና ዝናብ የቀላቀለ ከባድ አውሎ ነፋስ ባስከተለው የጎርፍ መጥለቅለቅ ሳቢያ እስካሁን የ49 ሰዎች ሕይዎት ማለፉ ተሰምቷል። በሄይቲ የ30 ሰዎች ሕይዎት ማለፉን እና ከ20 በላይ ሰዎች የገቡበት አለመታወቁን የሀገሪቱ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል። እስካሁን ያሉበት ሁኔታ ያልታወቁ ሰዎችን የመፈለጉ ሥራም መቀጠሉን ባለሥልጣናቱ ለአልጄዚራ ገልጸዋል።   ከዚሁ ጋር በተያያዘም የሟቾች ቁጥር ሊያሻቅብ እንደሚችል አመላክተዋል። እንዲሁም የአውሎ ነፋሱ ሰለባ በሆነችው ሌላኛው ሀገር ጃማይካ የ19 ሰዎች ሕይዎት ማለፉን ሮይተርስ ዘግቧል። እስካሁን ከተመዘገቡት በጣም ኃይለኛ የአትላንቲክ አውሎ ነፋሶች አንዱ እንደሆነ የተነገረለት ሃሪኬን ሜሊሳ በሠዓት 295 ኪሎ ሜትር እንደሚከንፍ ተገልጿል። አውሎ ነፋሱ የጃማይካን ምዕራባዊ ክልል በመምታት አስከፊ ጉዳት ማድረሱን የሀገሪቱ ባለሥልጣናት ተናግረዋል።   ሃሪኬን ሜሊሳ በካሪቢያን ቀጣና ኩባ፣ሄይቲ እና ጃማይካ በሰው ሕይወት እንዲሁም በንብረት ላይ የከፋ ጉዳት ማድረሱ ተሰምቷል። ይህን ተከትሎም በካሪቢያን የሚገኙ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ከኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት ውጭ መሆናቸውን ዘገባው አመላክቷል። የኤሌክትሪክ አቅርቦቱን ለመመለስና አካባቢዎቹንም የማጽዳት ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኙም ተጠቅሷል።
የአፍሪካ ህብረት የ30 ቢሊዮን ዶላር የአቪዬሽን መሰረተ ልማት የኢንቨስትመንት እቅድ ይፋ አደረገ
Oct 31, 2025 835
አዲስ አበባ፤ ጥቅምት 21/2018 (ኢዜአ):-የአፍሪካ ህብረት የአህጉሪቷን የአቪዬሽን መሰረተ ልማት ማዘመንን አላማ ያደረገ የ30 ቢሊዮን ዶላር የኢንቨስትመንት እቅድ ዛሬ ይፋ አድርጓል። ከጥቅምት 18 ቀን 2018 ዓ.ም አንስቶ በአንጎላ ሉዋንዳ ሲካሄድ የነበረው ሶስተኛው የአፍሪካ መሰረተ ልማት ፋይናንስ ጉባኤ ዛሬ ተጠናቋል። በጉባኤው ላይ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የአንጎላ ፕሬዝዳንት እና የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት ሊቀ መንበር ጆአኦ ሎሬንቾ፣ የህብረቱ ተቋማት አመራሮች፣ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች፣ የአየር መንገዶች ዋና ስራ አስፈጻሚዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። ከጉባኤው ጎን ለጎን በአፍሪካ ነጻ የአየር ትራንስፖርት ገበያ አማካኝነት የአህጉሪቷን አቪዬሽን መሰረተ ልማት በፋይናንስ በመደገፍ እና በማዘመን የተቀናጀ የአየር አገልግሎት እና ነጻ እንቅስቃሴን መፍጠር ላይ ያተኮረ ከፍተኛ የምክክር መድረክ ተከናውኗል። የአፍሪካ ህብረት የመሰረተ ልማት እና ኢነርጂ ኮሚሽነር ሌራቶ ማታቦጅ በመድረኩ ላይ በአየር ትራንስፖርት ገበያው አማካኝነት የአህጉሪቷን የአቪዬሽን መሰረተ ልማት ለማዘመን የሚውል የ30 ቢሊዮን ዶላር የኢንቨስትመንት እቅድ ዛሬ ይፋ አድርገዋል። እቅዱ አፍሪካ በቀጣይ 10 ዓመት የአቪዬሽን ዘርፉን ለማሻሻል የሚያስፈልጋትን ከ25 እስከ 30 ቢሊዮን ዶላር የፋይናንስ ክፍተት የሚሞላ እንደሆነ ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። በአፍሪካ እ.አ.አ በ2024 160 ሚሊዮን የነበረው የመንገደኞች መጠን እ.አ.አ በ2050 ወደ 500 ሚሊዮን ገደማ እንደሚደርስ የገለጸው ህብረቱ ኢንቨስትመንቱ የተሳፋሪዎችን ደህንነት ለማረጋገጥ እና አቅምን ለማጎልበት እንደሚያስችል አመልክቷል። በኢንቨስትመንት እቅዱ አማካኝነት ገንዘቡ ለአውሮፕላን ማረፊያ፣ አውሮፕላን ጣቢያ እና ጥገና ማዕከላት መሰረተ ልማት፣ የአቪዬሽን ስርዓቶች ማዘመን፣ ለሰው ኃይል ልማት፣ ለቁጥጥር ስራ፣ ለቴክኖሎጂ እና ተጓዳኝ ስራዎች እንደሚውል ተገልጿል። የአፍሪካ ህብረት 10 ቢሊዮን ዶላሩን ከአፍሪካ መንግስታት፣ ከቀጣናዊ የልማት ባንኮች እና ከባለቡዙ ወገን አጋሮች ለመሰብሰብ መታቀዱን አስታውቋል። ቀሪው 20 ቢሊዮን የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ አጋሮች፣ የሉዓላዊ ሀብት ፈንዶች (sovereign wealth funds) እና የጡረታ ፈንዶችን ጨምሮ ከግል እና የተቋማት ኢንቨስተሮች ለማግኘት መታሰቡን ነው ያመለከተው። የሀብት ማሰባሰቡ የሚከናወነው በአፍሪካ ነጻ የአየር ትራንስፖርት ገበያ ማዕቀፍ ሲሆን የ30 ቢሊዮን ዶላሩ ከእ.አ.አ 2025 እስከ 2035 ለሚተገበሩ ስራዎች የሚውል ነው። የአፍሪካ ህብረት የመሰረተ ልማት እና ኢነርጂ ኮሚሽነር ሌራቶ ማታቦጅ አቪዬሽን የትራንስፖርት አማራጭ ብቻ ሳይሆን የአፍሪካ ትስስር ስትራቴጂካዊ ሞተር እንዲሁም የአጀንዳ 2063 እና የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ቁልፍ አቅም ነው ብለዋል። በኢንቨስትመንት እቅዱ የሚሰሩ ፕሮጀክቶች ዓለም አቀፍ የአረንጓዴ ልማት መመዘኛዎችን ባሟላ እና ከካርቦን ልህቀት ነጻ በሆነ መልኩ እንደሚገነቡ አመልክተዋል። ህብረቱ ዘመናዊ፣ ውጤታማ እና ዘላቂ የአቪዬሽን ኔትወርክ በመፍጠር ለአፍሪካ የኢኮኖሚ ትስስር ለማጠናከር፣ የአየር ትራንስፖርት ግንኙነት ስር እንዲሰድ እና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት እንዲያድግ በቁርጠኝነት ይሰራል ነው ያሉት።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም