ቀጥታ፡
ዓለም አቀፍ ዜናዎች
ኢትዮጵያ 76ኛውን የዓለም ጤና ድርጅት ስብሰባ ታስተናግዳለች
Aug 5, 2026 459
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 29/2018 (ኢዜአ)፦ 76ኛው የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ ስብሰባ (RC76) ከነሐሴ 18 እስከ 22 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል። ስብሰባው ከዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ጽሕፈት ቤት ጋር በመተባበር የሚዘጋጅ ነው። በዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣና መረጃ መሠረት፣ ስብስባው የቀጣናውን የጤና አጀንዳዎች ላይ መምከርና አህጉራዊ ትብብርን ማጠናከርን ያለመ ነው። የ47ቱ የአፍሪካ ቀጣና አባል አገራት የጤና ሚኒስትሮች፣ ከፍተኛ ባለሥልጣናት፣ የዓለም አቀፍ ጤና መሪዎች፣ የልማት አጋሮች፣ ለጋሾችና የዓለም ጤና ድርጅት ተወካዮችን ጨምሮ ከ600 በላይ ተወካዮች በስብስባው ላይ ይሳተፋሉ። የስብሰባው ተሳታፊዎች በቀጣናዊ የጤና አቅዶች ላይ የተመዘገቡ ውጤቶችን የሚገመግሙ ሲሆን በአዳዲስ ስትራቴጂዎችና የውሳኔ ሀሳቦች ላይ ይመክራሉ። እንዲሁም የጤና ሥርዓቶችን ለማጠናከር፣ ሁለንተናዊ የጤና ሽፋን ተደራሽነትን ለማስፋፋት፣ የጤና ደህንነትን ለማሻሻልና የአደጋ ጊዜ ዝግጁነትን ለማሳደግ የሚረዱ የጋራ አቅጣጫዎችን ያስቀምጣሉ ተብሎ ይጠበቃል። በኢትዮጵያ፣ በአፍሪካ ህብረትና በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) የዓለም ጤና ድርጅት ተወካይ ፕሮፌሰር ፍራንሲስ ካሶሎ፤ ስብሰባው አባል አገራት የቀጣናውን የጤና አጀንዳ እንዲቀርጹ፣ አጋርነታቸውን እንዲያጠናክሩ እና በመላው አፍሪካ ጤናማ፣ አስተማማኝና ጠንካራ ማህበረሰቦችን የመገንባት ሂደት ለማፋጠን ትልቅ እድል የሚሰጥ ነው ብለዋል። ተወካዩ አክለውም የኢትዮጵያ ስብሰባውን ማስተናገድ፤ ለቀጣናዊ ወንድማማችነትና ለጋራ ትብብር ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል። ይህ አህጉራዊ ጉባኤ የኢትዮጵያን የጤና ሥርዓት ስኬቶች፣ በተለይም መሰረታዊ የጤና አገልግሎቶችን በማስፋፋትና በቅርቡ በክልል የተከሰተውን በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ተከስቶ የነበረውን የማርበርግ ቫይረስ በመቆጣጠር ረገድ የተመዘገቡ ውጤቶችን ለማሳየት ዕድል እንደሚፈጥር መረጃው አመልክቷል። ስብስባው የአፍሪካ ህብረትና የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን (UNECA) መቀመጫ የሆነችው አዲስ አበባ፣ የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷን በመጠቀም ለጋራ የጤና ፈተናዎች የተቀናጀ አህጉራዊ ምላሽ ለመስጠት ስትራቴጂካዊ መድረክ እንድትሆን ያደርጋታል። በስብስባው ላይ የቴክኒክ ውይይቶች፣ አውደ ርዕዮች ፣ የሁለትዮሽ ስብሰባዎችና የሕዝብ ግንኙነት ስራዎች የሚካሄዱ ሲሆን፣ እነዚህም በአፍሪካ ተቋማት መካከል የጤናው ዘርፍ የፈጠራ ስራዎችንና የእውቀት ልውውጥን የሚያጎሉ እንደሚሆኑ ተገልጿል። የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ቀጣናዊ ኮሚቴ የቀጣናዊ ጽሕፈት ቤቱ የበላይ አካል ሲሆን፤ በየዓመቱ በመሰብሰብ የቀጣናውን የጤና ፖሊሲ ይወስናል፣ የድርጅቱን ሥራዎች ይገመግማል፣ እንዲሁም በመላው አህጉሪቱ ለሚከናወኑ የጤና ተግባራት ቅድሚያ የሚሰጣቸውን አጀንዳዎች ያስቀምጣል።
ኢትዮጵያ የማዕድን ሀብቷን ቀጣዩ የኢኮኖሚዋ ምሰሶ እያደረገች ነው- ሲኤንኤን
Aug 4, 2026 480
የሲኤንኤን ጋዜጠኛ ቪክቶሪያ ሩቢዳሪ በኢትዮጵያ ላይ በሚያተኩረው ዘገባዋ በሀገሪቱ ኮረብቶች ያለውን ወርቅ ጨምሮ ከፍተኛ የብረት ማዕድናት አምራች ለመሆን እያደረገች ያለውን ጥረት መመልከቷን ተናግራለች። በዘገባዋ ኢትዮጵያ በማዕድን ዘርፍ ከፍተኛ የሃይል ሚዛን መሆን እንደምትፈልግ ገልጻ፤በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሚገኘው ኩርሙክ የወርቅ ፕሮጀክት በኢትዮጵያ የማዕድን ኢንቨስትመንቶች ውስጥ በዋናነት የሚጠቅስ መሆኑን ተናግራለች። በምዕራብ ኢትዮጵያ አረንጓዴ ከለበሱት ከፍተኛ የኮረብታ ስፍራዎች ላይ በቢሊዮኖች የሚቆጠሩ ዶላሮችን የሚያስገኙ ከፍተኛ የወርቅ ሀብቶች እንዳሉ እና አዳዲስ ኢንዱስትሪዎች ብቅ እያሉ መሆኑን ትናገራለች። በሺዎች የሚቆጠሩ የግንባታ ባለሙያዎች እና ማዕድን አውጪዎች በኢትዮጵያ ግዙፍ የሆነውን የወርቅ ማዕድን ፋብሪካ ግንባታ እያከናወኑ እንደሚገኝ ገልጻለች። በስፍራው የሚገኙ የማዕድን እና ጂኦሎጂ ባለሙያዎች የወርቅ ማዕድኑን የማጣራት ስራ እያከናወኑ መሆኑን ገልጻለች። ጋዜጠኛዋ የወርቅ ማጣራት እና ምርት ሂደቱን በተመለከተ ከባለሙያዎች ማብራሪያ ማግኘቷንም አመልክታለች።   ወርቁን የማግኘት ሂደቱ እጅጉን ፈታኝ እና አድካሚ እንደሆነ ገልጻ፥ይሁንና ልፋቱ ትልቅ ጠቀሜታ የሚያስገኝ መሆኑን ተናግራለች። የወርቁን ግብአት ውጪ ሀገር ልኮ ከማጣራት ይልቅ በኩርሙክ የወርቅ ማዕድን ፋብሪካ የራሱ ማጣሪያ ፕላንት እንዳለው በጉብኝቷ ወቅት መረዳቷን አመልክታለች። የሲኤንኤኗ ጋዜጠኛ ቪክቶሪያ ሩቢዳሪ ወርቅ የሀገሪቷ ዋና የወጪ ንግድ ገቢ ምንጭ እየሆነ መምጣቱን ገልጻለች። ባለፈው ዓመት በወርቅ የተገኘው የወጪ ንግድ ገቢ ከፍተኛ መሆኑን ተናግራለች። ይህም የኢትዮጵያን የኢንዱስትሪ ውጥኖች በግልጽ የሚያሳይና ኢትዮጵያ የማዕድን ሀብቷን ቀጣዩ የኢኮኖሚዋ ምሰሶ እያደረገች እንደምትገኝ ሲኤንኤን በዘገባው አስረድቷል።
የኤልኒኖ አየር ንብረት ክስተትን ለመቋቋም አህጉራዊ የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን ማጠናከር ይገባል
Jul 30, 2026 772
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 23/2018 (ኢዜአ)፦የኤልኒኖ አየር ንብረት ክስተትን ለመቋቋም አህጉራዊ የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ ተመለከተ፡፡ የአፍሪካ ህብረት በፓሲፊክ ውቅያኖስ ሙቀት የሚፈጠር የአየር ንብረት መዛባት (ኤልኒኖ) አስመልክቶ አስቸኳይ ስብስባውን ዛሬ በአዲስ አበባ እያካሄደ ይገኛል። በህብረቱ የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ውሃ እና ከባቢ አየር (ADREE) ልዩ የቴክኒክ ኮሚቴ የተዘጋጀው ስብሰባ እ.አ.አ በ2026 ይከሰታል ተብሎ የሚጠበቀውን የኤልኒኖ አየር ንብረት ክስተት ለመቋቋም እና አህጉራዊ የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን ማጠናከርን ያለመ ነው። ከፍተኛ የምክክር መድረኩ "የአፍሪካን ቅድመ ዝግጅት፣ የመቋቋም አቅም እና የአየር ንብረት እርምጃዎችን ማጠናከር" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ይገኛል። በስብሰባው ላይ በአካል ከተገኙት ተሳታፊዎች በተጨማሪ በበይነ መረብ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በሁነቱ ላይ ታድመዋል። የስብሰባው ዋና ትኩረት አፍሪካ ለኤልኒኖ የተቀናጀ ምላሽ እንድትሰጥ የጋራ ትብብርን መፍጠር ነው። በተጨማሪም በ31ኛው እና በ32ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንብረት ለውጥ ዓለም አቀፍ ጉባኤዎች (COP31) እና (COP32) ላይ የአፍሪካን ሚና ማሳደግ እና የአህሪቷን አጀንዳዎች ጎልተው እንዲታዩ ማድረግ በሚቻልባቸው ሁኔታዎች ላይም ይመክራል። ለአንድ ቀን የሚቆየው ስብስባ በባለሙያዎች እና በሚኒስትሮች ደረጃ ተከፍሎ ይካሄዳል። የአፍሪካ የሜቲዎሮሎጂ ትግበራዎች ልማት ማዕከል (ACMAD) የኤልኒኖ ክስተትን ትንበያ እና በአህጉሪቱ ላይ ሊያስከትል የሚችለውን ተፅዕኖ በተመለከተ ጥናታዊ ፅሁፍ ያቀርባል። በተጨማሪም በአየር ንብረት ለውጥ የአፍሪካ ተደራዳሪዎች ቡድን መሪነት አህጉሪቱ በመጪዎቹ ዓለም አቀፍ የአየር ንብረት ጉባኤዎች የምታደርገው ተሳትፎ እና ለዓለም አቀፉ የአደጋ ስጋት ቅነሳ ጉባኤ የሚደረጉ ዝግጅቶች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል። የአፍሪካ የውሃ ሚኒስትሮች ምክር ቤትም (AMCOW) ከ 2026 የአፍሪካ ህብረት የዓመቱ መሪ ሀሳብ ጋር የተያያዘ ሪፖርት ያቀርባል። የአባል ሀገራት ሚኒስትሮችም ስለ ኤልኒኖ ተፅዕኖ እና አህጉራዊ ምላሽ መግለጫዎችን ይሰጣሉ ተብሎ ይጠበቃል። ስብሰባው በኤልኒኖ ዙሪያ የተዘጋጀውን የድርጊት መርሃ ግብር፣ የባለሙያዎች ሪፖርት እና የጋራ የአቋም መግለጫ እንደሚያፀድቅም ተመላክቷል። በስብሰባው ከአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት በተጨማሪ የተለያዩ አጋር አካላት ተገኝተዋል። ኤልኒኖ (El Nino) በፓሲፊክ ውቅያኖስ የውሃ ሙቀት ከመደበኛው በላይ በመጨመሩ ምክንያት የሚከሰት ዓለም አቀፋዊ የከባቢ አየርና የአየር ንብረት መዛባት ክስተት ነው። የኤልኒኖ ተጽእኖ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያልተለመደ የከፋ ድርቅን፣ ከፍተኛ የጎርፍ አደጋንና የሙቀት መጠን መጨመርን በማስከተል በግብርና እና በሰዎች ሕይወት ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳል።
ሀገራት የአፍሪካ ህብረትን የፋይናንስ ነጻነት ለማረጋገጥ የተጠናከረ ድጋፍ ማድረግ ይገባቸዋል - አምባሳደር ኤድዋርድ ቢዚማና
Jul 29, 2026 1254
አዲስ አበባ ፤ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሀገራት የአፍሪካ ህብረት የፋይናንስ ነጻነት ለማረጋገጥ የተጠናከረ ድጋፍ እንዲያደርጉ የብሩንዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ሰብሳቢ አምባሳደር ኤድዋርድ ቢዚማና ጥሪ አቀረቡ። በአዲስ አበባ ለሁለት ቀናት ሲካሄድ የቆየው እና የህብረት አባል ሀገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች የተሳተፉበት 49ኛው የአፍሪካ ህብረት ስራ አስፈፃሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ተጠናቋል። የምክር ቤቱ ስብሰባ “ ዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ደኅንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ሥርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚለው የ2026 የህብረቱ ዓመታዊ መሪ ሀሳብ አማካኝነት ተከናውኗል። የብሩንዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ሰብሳቢ አምባሳደር ኤድዋርድ ቢዚማና ባደረጉት የመዝጊያ ንግግር ምክር ቤቱ አጀንዳ 2063 እና የህብረቱ መሪ ሀሳብን ጨምሮ በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ መምከራቸውን ገልጸዋል። የአፍሪካ ሀገራት አጀንዳ 2063 ለማሳካት እና የእርስ በእርስ ትብብራቸውን ለማጠናከር በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ ማረጋገጣቸውን አመልክተዋል። በፓን አፍሪካኒዝም መንፈስ አህጉራዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመስራት ያሳዩት ፍላጎት አበረታች መሆኑንም ተናግረዋል። ኢትዮጵያ እና ኬንያ ለአፍሪካ ህብረት ዓመታዊ በበጎ ፈቃደኝነት ተጨማሪ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ይፋ ማድረጋቸው የፋይናንስ ነጻነትን ማረጋገጥ የሚያስችል እርምጃ መሆኑን ገልጸዋል። ሌሎች የህብረቱ አባል ሀገራት የኢትዮጵያንና የኬንያን ፈለግ በመከተል ተመሳሳይ እርምጃ እንዲወስዱ ጥሪ አቅርበዋል። ሀገራት የገቧቸውን ቃል ኪዳኖችና ስምምነት የደረሱባቸውን ጉዳዮች በሚገባ መተግበር እንዳለባቸውም ነው ያስገነዘቡት። ኢትዮጵያ የምክር ቤቱ ስብሰባ በስኬት እንዲጠናቀቅ እንዲሁም ለሚኒስትሮችና ሌሎች ልዑካን ላደረገችው አቀባበልም አመስግነዋል።
49ኛው የአፍሪካ ህብረት ስራ አስፈፃሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ተጠናቀቀ
Jul 29, 2026 1089
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 22/2018(ኢዜአ)፦ ከትናንት ጀምሮ በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው 49ኛው የአፍሪካ ህብረት ስራ አስፈፃሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ዛሬ ተጠናቋል። የምክር ቤቱ ስብሰባ “ ዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ደኅንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ሥርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚለው የ2026 የህብረቱ ዓመታዊ መሪ ሀሳብ አማካኝነት ተከናውኗል። በአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን አዘጋጅነት የተካሄደው የሁለት ቀናት ስብሰባ ላይ የህብረት አባል ሀገራት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ተሳትፈዋል። ሚኒስትሮቹ ቅድሚያ በሚሰጣቸው ቁልፍ አጀንዳዎችና የአፍሪካን አህጉራዊ ትስስር ማፋጠን በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል። በስብሰባው ሚኒስትሮቹ የአጀንዳ 2063 አፈፃፀም የሚከታተለውን ኮሚቴ ሪፖርት እንዲሁም የቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት እና በአሁኑ የአፍሪካ ህብረት ወቅት ያሉ ስምምነቶችና የአሰራር ማዕቀፎች ያሉበትን የትግበራ ደረጃ ገምግመዋል። በተጨማሪም የ2026ቱን የህብረቱን የዓመቱ መሪ ሀሳብ የእስካአሁን የአፈጻጸም ሂደት ላይም መክረዋል። ስብሰባው እ.አ.አ. በ2017 በህብረቱ አባል ሀገራትና መንግስታት መሪዎች የፀደቀውን ተቋማዊ ማሻሻያ መነሻ ያደረገ ነው። ከስብሰባው የተገኙ ውጤቶች አህጉራዊ ዘላቂ ልማትን፣ ትስስርና ብልፅግናን እውን ለማድረግ የተቀረፀውን የአፍሪካ ህብረት የረጅም ጊዜ መሪ እቅድ (አጀንዳ 2063) ስኬታማ ለማድረግ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ይኖራቸዋል ተብሎ ይጠበቃል።
አፍሪካ ከውጭ የፋይናንስ ጥገኝነት በመላቀቅ የውስጥ የገቢ አቅሟን በአግባቡ መጠቀም ይጠበቅባታል 
Jul 28, 2026 559
አዲስ አበባ ፤ሐምሌ 21/2018(ኢዜአ)፦ አፍሪካ ዘላቂ ልማቷን ለማረጋገጥ ከውጭ የፋይናንስ ጥገኝነት ተላቃ የውስጥ የገቢ አቅሟን በአግባቡ መጠቀም እንዳለባት የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን ዋና ፀሀፊ ክሌቨር ጋቴቴ ገለጹ። 49ኛው የአፍሪካ ህብረት የሥራ አስፈፃሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። የምክር ቤቱ ስብሰባ “ዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ደኅንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ሥርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚለው የ2026 የህብረቱ ዓመታዊ መሪ ሀሳብ አማካኝነት ይከናወናል። የኢፌዴሪ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር)፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የብሩንዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የሥራ አስፈጻሚ ምክር ቤቱ ሰብሳቢ ኤድዋርድ ቢዚማና፣ የአባል ሀገራት ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች፣ ዲፕሎማቶች እና ሌሎች እንግዶች በስብሰባው መክፈቻ ላይ ተገኝተዋል።   የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን ዋና ፀሀፊ ክሌቨር ጋቴቴ እንደገለጹት፤ በአሁኑ ወቅት የጂኦፖለቲካ ውጥረቶች፣ የግጭቶች መበራከት፣ የብድር ክፍያ ጫና እና የፋይናንስ አቅርቦት እጥረት በአህጉሪቷ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እያሳደሩ ይገኛሉ። እነዚህን ፈተናዎች ለመወጣት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን አባል ሀገራት የታክስ ስርዓታቸውን እንዲያዘምኑ ጠቁመው፤ ኮሚሽኑ የሀገር ውስጥ ካፒታል ገበያዎችን እንዲያጠናክሩ ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። አህጉሪቷ በየዓመቱ በሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር ሳቢያ በርካታ ገንዘብ እንደምታጣና የታክስ መሰብሰብ አቅሟም ከአጠቃላይ ሀገራዊ ምርቷ 16 በመቶ ብቻ መሆኑን አመልክተው፤ ይህ አሰራር በአስቸኳይ መለወጥ እንዳለበትም ተናግረዋል። በግብርና፣ በኃይል፣ በኢንዱስትሪ እና በአየር ንብረት መከላከል የተቀናጀ ፖሊሲና አሰራር መከተል እንደሚገባ ገልጸዋል። የሀገር ውስጥ ቁጠባና ኢንቨስትመንትን ለአህጉሪቱ ልማት ማዋል እና ሕገ-ወጥ የገንዘብ ማሸሽን መግታት እንደሚገባ ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የአፍሪካ እርስ በርስ ንግድ 17 በመቶ ብቻ ሲሆን፤ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ሙሉ በሙሉ ሲተገበር በ2045 የውስጥ ንግድን እንደሚያሳድግ ተናግረዋል። የአየር ንብረት ለውጥን ለመቋቋም፣ የመረጃ ስርዓቶችን ለማዘመንና ዲጂታል መሠረተ-ልማቶችን ለማስፋፋት መዋዕለ-ነዋይ ማፍሰስ እንደሚገባም ገልጸዋል።
አፍሪካ አጀንዳዎቿን ለማስፈጸም የራሷን ሀብት መጠቀም ላይ ትኩረት ማድረግ አለባት
Jul 28, 2026 274
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 21/2018 (ኢዜአ)፦ አፍሪካ አጀንዳዎቿን ለማስፈጸምና ግቦቿን ለማሳካት የራሷን ሀብት መጠቀም ላይ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባት የብሩንዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት ሰብሳቢ ኤድዋርድ ቢዚማና ገለጹ። 49ኛው የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው። ስብሰባው እየተደረገ ያለው “ዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ደኅንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ሥርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በሚል መሪ ሀሳብ ነው። የብሩንዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የአፍሪካ ህብረት ስራ አስፈፃሚ ምክር ቤት ሰብሳቢ ኤድዋርድ ቢዚማና አፍሪካ በጋራ ጉዳዮቿ ላይ በአንድ ድምፅና በተባበረ ክንድ መቆም እንዳለባት አስገንዝበዋል። ሚኒስትሩ አፍሪካውያን ሁለንተናዊ ጥቅሟን ለማረጋገጥ በፓን-አፍሪካኒዝም እሴቶች ላይ የተመሠረተ ጠንካራ የጋራ አንድነት መገንባት አለባት ብለዋል። በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ማሻሻያ ላይ የአፍሪካ ሀገራት የጋራ አቋም የያዙባቸውና የህብረቱ ማዕቀፎች በሚገባ መተግበርና አፈጻጸማቸውን መከታተል እንደሚገባም አመልክተዋል። ማዕቀፎቹ የአፍሪካን ፍላጎት በዓለም አቀፍ መድረክ ለማስከበር ዋና መደላድል መሆናቸውን ነው የገለጹት። የህብረቱን ዘላቂ የፋይናንስ ምንጭ በተመለከተ ሚኒስትሩ እንደገለጹት፣ አፍሪካ የራሷን አጀንዳዎች ለማስፈጸምና በውሳኔ አሰጣጥ ላይ ነፃነቷን ለማስጠበቅ የራሷን ሀብት መጠቀም ላይ ትኩረት ማድረግ አለባት ብለዋል ሚኒስትሩ። በዚህ ረገድም የአፍሪካ ሀገራት የፋይናንስ ድጋፋቸውን ማድረግ እንዳለባቸው ነው ጨምረው የተናገሩት። ስምምነት እና መግባባት (Consensus) የፖለቲካ ብስለት እንጂ የድክመት ምልክት እንዳልሆነ ጠቁመው ይህም የአፍሪካ ሀገራትን የሚያቀራርቧቸውን የጋራ እሴቶች እንዲፈልጉ የሚያስችል ዋና መሳሪ ነው ብለዋል። የተያዙ አጀንዳዎችንና የተገቡ ቃል ኪዳኖችን ለአፍሪካውያን ህይወት ለውጥ ወደሚያመጡ ተጨባጭ ውጤቶች መቀየር እንደሚያስፈልግም አስገንዝበዋል።
የአፍሪካ ሀገራት የልማት ግቦችን የሚያሳኩ የአሰራር ማዕቀፎችን በፍጥነት ወደ ስራ ማስገባት ይጠበቅባቸዋል
Jul 28, 2026 204
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሀገራት አህጉራዊ የልማት ግቦችን እውን የሚያደርጉ ስምምነቶችን በአፋጣኝ አፅድቀው ወደ ትግበራ እንዲያስገቡ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ጥሪ አቀረቡ። 49ኛው የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ዛሬ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል።   የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በዚሁ ወቅት እንዳሉት አፍሪካ በመካከለኛው ምስራቅ ከቀጠለው ግጭት ጋር ተያይዞ የሚመጡ አሉታዊ ተፅዕኖዎችን በሙሉ አቅሟ እየተጋፈጠች ነው። የግጭቱ መቀስቀስ የዓለም አቀፍ የአቅርቦት መስመሮችን በማስተጓጎሉ ምክንያት የነዳጅ፣ የሸቀጣሸቀጥ እና የመሰረታዊ ቁሳቁሶች ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ እንዲያሻቅብ ማድረጉን ገልጸዋል። የአፍሪካ ህብረት ባለሙያዎች ጉዳዩን በጥልቀት ሲመረምሩት እንደቆዩና የዚህ ቀውስ ዳፋ ለበርካታ አመታት አብሮን ሊቆይ እንደሚችል ማስጠንቀቂያ መስጠታቸውን አብራርተዋል። በሌላ በኩል በአህጉሪቱ እየተስፋፋ ያለው የሽብርተኝነት አደጋ እና የጤና ስጋት አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ሊቀ መንበሩ አውስተዋል። በሳህል ቀጣና ባደረጉት ጉብኝት የሰብአዊ ሁኔታዎችን መመልከትና ሽብርተኝነትን በጋራ መከላከል የሚያስችል ቀጣናዊ ትብብር ለማጠናከር ጥረት ማድረጋቸውን ገልጸዋል። የአፍሪካ የበሽታ መከላከያና መቆጣጠሪያ ማዕከል (Africa CDC) እያከናወነ ላለው ስራ ላይ አባል ሀገራት ድጋፋቸውን እንዲያጠናከሩም ጠይቀዋል። ሊቀ መንበሩ በአፍሪካ ህብረት የበጀት እና አደረጃጀት ላይ በሰጡት ማብራሪያም የ2027 የበጀት ረቂቅ 797 ሚሊየን 893 ሺህ 884 ዶላር መሆኑን ይፋ አድርገዋል። ይህ በጀት ከአባል ሀገራት መደበኛ መዋጮ እና በዓለም አቀፍ አጋሮች የሚሸፈን መሆኑን ጠቁመዋል። የአጀንዳ 2063 ሁለተኛውን የ10 ዓመት እቅድ ለማስፈጸም ወደ ሁለት ቢሊየን ዶላር ገደማ ፋይናንስ እንደሚያስፈልግ ነው ሊቀ መንበሩ ያስረዱት። ኮሚሽኑ ለአፍሪካ ልማት የሚሆን የግል እና የህዝብ ካፒታልን መሳብ የሚያስችሉ ፖለቲካዊ እና ተቋማዊ ሁኔታዎችን የማመቻቸት ሚናውን እንደሚወጣም ተናግረዋል። አባል ሀገራትም የህብረቱን የልማት ግቦች እውን ለማድረግ ቁልፍ የሆኑ ህጋዊ ስምምነቶችንና ሰነዶችን በፍጥነት እንዲያፀድቁ ጥሪ አቅርበዋል።
የአፍሪካን አንድነት የበለጠ በማጎልበት የበለፀገች አህጉር መገንባት አለብን-መሐሙድ አሊ ዩሱፍ
May 25, 2026 20579
አዲስ አበባ፤ግንቦት 17/2018 (ኢዜአ)፦የአፍሪካን አንድነት የበለጠ በማጎልበት የበለፀገች አህጉር መገንባት እንደሚያስፈልግ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። 63ኛው የአፍሪካ ቀን ''የ63 ዓመታትን ዓመታት አንድነት፣ ትስስርና ልማት፤ አብረን እናክብር” በሚል መሪ ሃሳብ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ህብረት ቅጥር ግቢ በተለያዩ ሁነቶች እየተከበረ ይገኛል። በዝግጅቱም የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ ጨምሮ የሕብረቱ አባል ሀገራት ዲፕሎማቶችና ተጋባዥ እንግዶች ታድመዋል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ አፍሪካ በዓለም መድረክ ያላት ሚና በየ ጊዜው እየታደሰ መምጣቱን ገልጸዋል። የአህጉሪቷ የሕዝብ ቁጥርና የኢኮኖሚ ዕድገትም በጥቂት ዓመታት ውስጥ የአፍሪካን ጥቅል የሀገር ውስጥ ዕድገት ምጣኔ 10 ትሪሊዮን ዶላር ያደርሰዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል። የአፍሪካ ወጣቶችም ሌሎች አህጉራት ጭምር የሚመኟቸው የአህጉሪቷ ዕድገትና ብልፅግና አቅም መሆናቸውን አንስተዋል። በቀጣይም የአፍሪካዊያንን የአንድነት ኃይል የበለጠ በማጎልበት የአህጉሪቱን ዕምቅ ፀጋዎች ለሁለንተናዊ ዕድገትና ብልፅግና መቀየር እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ በበኩላቸው፥የአፍሪካዊያን ባህልና ዕሴት ለአህጉሪቷ መፃኢ ዕድል፣ ዕድገትና ብልፅግና የሚተርፍ የጥንካሬ ምንጭ ነው ብለዋል። የአፍሪካን የትብብር አቅም በማጎልበት የአህጉሪቷ ዜጎችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥና የራስን የተሻለ ዕድል መቅረፅ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። ለዚህም በሁሉም ዘርፍ የአፍሪካን የኢኮኖሚ ዕድገት በማስፋት የአህጉሪቱን ዕምቅ የልማት ፀጋ ወደ ዘላቂ ብልፅግና መቀየር እንደሚገባ ተናግረዋል። በአህጉሪቷ ላይ የደረሱ በደሎች ፍትሕ እንዲያገኙ ከማድረግ ባሻገርም ለአጀንዳ 2063 ስኬት በቁርጠኝነት በመስራት የወደፊት እጣ ፋንታ መወሰን እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። በየዓመቱ የአፍሪካ ቀን መከበር የጀመረው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁን የአፍሪካ ህብረት እ.ኤ.አ በ1963 መመስረቱን እንደሆነ ይታወቃል። የዘንድሮው የአፍሪካ ቀንም የህብረቱ ኮሚሽን ከህብረቱ ሰራተኞች ማኅበር፣ አባል ሀገራት፣ ከህብረቱ አደረጃጀቶችና ቀጣናዊ የኢኮኖሚ ማህበረሰቦች ጋር በመተባበር ተዘጋጅቷል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የአፍሪካ ሕብረት ለታዳጊው ዓለም የፍትህ ድምፅ እና ለባለብዙ ወገን ግንኙነት ዋነኛ መገለጫ ነው
May 13, 2026 13336
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሕብረት ለታዳጊው ዓለም የፍትህ ድምፅ እና ለባለብዙ ወገን ግንኙነት ዋነኛ መገለጫ መሆኑን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ገለጹ፡፡ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በሰላም፣ በጸጥታ፣ በዘላቂ ልማት እና በሰብአዊ መብቶች ዙሪያ ያላቸውን ትብብር ይበልጥ ተቋማዊ ለማድረግ የሚያስችል ስምምነት ተፈራርመዋል። ስምምነቱን የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ፈርመውታል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በዚሁ ወቅት በሰጡት መግለጫ፣ የአፍሪካ ህብረት ለታዳጊው ዓለም የፍትህ ድምፅ እና ለባለብዙ ወገን ግንኙነት ዋነኛ መገለጫ መሆኑን ገልጸዋል። አጋርነታቸውን ይበልጥ ተቋማዊ የሚያደርገው ይህ ስምምነት በቁልፍ ዘርፎች ላይ የተመዘገቡ ስኬቶችንና የወደፊት ዕቅዶችን መነሻ ያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። አፍሪካ በተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ውስጥ በቋሚ አባልነት አለመካተቷን ታሪካዊ ኢ-ፍትሃዊነት ነው ያሉት ዋና ጸሐፊው፣ ይህም የምክር ቤቱን ተቀባይነትና ውጤታማነት እንደሚጎዳው አስገንዝበዋል። በተጨማሪም ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ሥርዓት ሊስተካከል እንደሚገባ ጠቅሰው አፍሪካ ከጥሬ ዕቃ አቅራቢነት ወጥታ ለአረንጓዴ ኢነርጂ ሽግግር የማምረቻና የማጣሪያ ማዕከል መሆን እንዳለባት ጠቁመዋል፡፡ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በበኩላቸው፣ የአፍሪካ ህብረት የ2063 አጀንዳ እና የተባበሩት መንግሥታት የ2030 አጀንዳ የተጣጣሙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በአፍሪካ ቀንድ ያሉ ፈተናዎችን ለመፍታት በቅርበት እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ሥርዓት ማሻሻያ ተደርጎ የአፍሪካ ሀብቶች ጥቅም ላይ እንዲውሉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ በናይሮቢ የተካሄደው የ"አፍሪካ ፎርዋርድ" (Africa Forward) ጉባኤ ውጤቶች ክትትል እንዲደረግባቸው አሳስበዋል፡፡ አፍሪካ በፀጥታው ምክር ቤት ውስጥ ድምጽን በድምጽ የመሻር መብትን ጨምሮ ቋሚ መቀመጫና ፍትሃዊ ውክልና እንዲኖራት የሚለውን የአህጉሪቱን ጥያቄ በድጋሚ አረጋግጠዋል። ይህ ስምምነት በሁለቱ ድርጅቶች መካከል ያለውን ስልታዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚያሸጋግረው ይጠበቃል። 10ኛው የአፍሪካ ህብረት እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የከፍተኛ ደረጃ ውይይት ዛሬ በአዲስ አበባ መካሄዱ ይታወቃል፡፡
አፍሪካ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዳይኖራት ማድረግ የዓለም አቀፍ ተቋማትን ኢ-ፍትሐዊነት የሚያንጸባርቅ ነው
May 13, 2026 12157
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2018(ኢዜአ)፦ አፍሪካ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዳይኖራት ማድረግ የዓለም አቀፍ ተቋማትን ኢ-ፍትሐዊነት የሚያንጸባርቅ ተግባር መሆኑን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሀፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ ገለጹ። የአፍሪካ ሕብረትና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት 10ኛ ዓመታዊ ኮንፍረንስ በአፍሪካ ሕብረት እየተካሄደ ነው። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሀፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ የመንግስታቱ ድርጅት በሁሉም ዘርፎች ቀዳሚ ተግባር አፍሪካን የማድረግ የፖለቲካም ሆነ የሞራል ግዴታ አለበት። አፍሪካ አህጉራዊ ግጭቶችን በማርገብ፣ አህጉራዊ ዕድገትና ብልፅግናን ለማረጋገጥ የምታደርገው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን በመግለጽ፤ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣናና ሌሎች የሰላምና ጸጥታ ኢኒሼቲቮች አስደናቂ መሆናቸውን ገልጸዋል። አፍሪካ በዓለም ሁለንተናዊ እንቅስቀሴ ላይ ያላት ሚና የጎላ መሆኑን እንገነዘባለን ያሉት ዋና ጸሀፊው፤ በታሪክና በዓለም ኢ-ፍትሐዊ አሰራር የደረሰባትን በደል ለመቀልበስ የምታደርገውን ጥረት ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ በርካታ የአፍሪካ ሀገራት ከቅኝ ግዛት ባልወጡበት ወቅት የተቋቋሙ ዓለም አቀፍ ተቋማት አህጉሪቱ በፀጥታው ምክር ቤት ቋሚ መቀመጫ እንዳይኖራት ማድረጋቸው ተገቢ አለመሆኑን ገልጸዋል። አፍሪካ ባልተሳተፈችበት የተቋቋሙ የዓለም አቀፍ ተቋማት ኢ-ፍትሐዊነት አፍሪካን ብዙ አሳጥቷታል ያሉት ዋና ጸሀፊው፤ አፍሪካዊ ችግሮችን በአፍሪካ ለመፍታት የተጀመሩ ኢንሼቲቮችን መደገፍ እንደሚገባ ተናግረዋል። የመንግሥታቱ ድርጅት አፍሪካዊ ግጭቶች በአፍሪካ ማዕቀፍ እንዲፈቱ በመሪነት ከመሳተፍ ባለፈ የአፍሪካ ሕብረትን ጥረት እንደሚደግፍ ጠቁመዋል። አፍሪካ በወሳኝ ማዕድናትና በአረንጓዴ ኢኮኖሚ ትልቅ አቅም እንዳላት ገልጸው፤ ሀብቷን እሴት በመጨመር ለዓለም ገበያ የምታቀርብበትን መንገድ መቀየስ ይገባል ብለዋል።
አፍሪካ ለ2030 እና አጀንዳ 2063 ግቦች የሚያስፈልጋትን የልማት ፋይናንስ ለማግኘት የራሷን የብድር ደረጃ መመጠኛ ተቋም ለማቋቋም ወሰነች
May 13, 2026 12022
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2018(ኢዜአ)፦ አፍሪካ ለ2030 እና አጀንዳ 2063 ግቦች የሚያስፈልጋትን የልማት ፋይናንስ ለማግኘት የተዛባውን የዓለም የፋይናንስ ስርዓት የሚያጣጥም የራሷን የብድር ደረጃ መመጠኛ ተቋም (African Rating Agency) ለማቋቋም መወሰኗን የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። የአፍሪካ ሕብረትና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት 10ኛ ዓመታዊ ኮንፍረንስ በአፍሪካ ሕብረት አዳራሽ እየተካሄደ ነው። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ መድረኩ በአፍሪካ ሰላምና ጸጥታ፣ ዘላቂ ልማት፣ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ አስተዳደርና በተለዋዋጭ ዓለም የአፍሪካ ፈተናዎች ዙሪያ የሚያተኩር ነው።   የመካከለኛው ምስራቅ ጦርነትን ጨምሮ የዓለም ነባራዊ ሁኔታ በአሕጉሪቱ ላይ የሚያደርሰውን ተፅዕኖ ለመቋቋም የሚደረግ ጥረት ቢኖርም በሚሊየን የሚቆጠሩ ሰዎች የሚሰቃዩበትና የሚሰደዱበት አስቸጋሪ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። ይሄውም በአፍሪካ አስተማማኝና ዘላቂ መፍትሔ ለማበጀት በሚደረገው ጥረት ላይ እንቅፋት እየፈጠረ መሆኑን በመጥቀስ፣ ከጸጥታ ባለፈ በመልካም አስተዳደር፣ በልማትና የማይበገር ኢኮኖሚ በመገንባት አስቻይ ሁኔታ መፍጠር እንደሚገባ ገልጸዋል። በአፍሪካ የልማት ፋይናንስ አሳሳቢ ጉዳይ መሆኑን የገለጹት የኮሚሽኑ ሊቀ መንበር፤ ዓለም አቀፉ የፋይናንስ አስተዳደር የአጀንዳ 2063 እና 2030 ግቦችን ለማሳካት እንቅፋት ፈጥሯል ብለዋል። በተለይም ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የተቋቋሙና አሁንም ያለው ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ስርዓት ለአፍሪካ ፍላጎትና እውነታ ምላሽ የማይሰጥ መሆኑንም ተናግረዋል። በመሆኑም አፍሪካን ከዓለም አቀፉ የፋይናንስ ስርዓት ጋር ለማጣጣም የራሷን የብድር ደረጃ መመጠኛ ተቋም (Africa Rating Agency) ለማቋቋም መወሰኗን ገልጸዋል። ይሄውም የአፍሪካ ሕብረት በጉዳዩ ላይ በጥልቀት ሲሰራ ቆይቶ እ.አ.አ በመጪው ሰኔ ወር 2026 በሞሪሼስ በይፋ እንደሚጀመር አስታውቀዋል። የመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በአፍሪካ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደሩን ገልጸው፤ በብዙ ሀገራት የምግብ ሸቀጦች ዋጋ ንሯል፤ በአንዳንድ ሀገራት የነዳጅ ዋጋ ከ100 እስከ 150 በመቶ ጨምሯል ነው ያሉት። የአፍሪካ ሕብረት ከተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጋር በትብብር ሲሰራ መቆየቱን በመጥቀስ፣ የእርስ በርስ ትብብሩን ለማጠናከር በቅርበት እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል። ሁለቱ ተቋማት አጋርነታቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው በመግለጽ፤ በተቋማቱ መካከል ያለውን ዘርፈ ብዙ ትብብር ወደፊት ማሻገር ያስፈልጋል ብለዋል።
የአፍሪካ ህብረት እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የከፍተኛ ደረጃ ውይይት በአዲስ አበባ ይካሄዳል
May 13, 2026 1926
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2018(ኢዜአ)፦ 10ኛው የአፍሪካ ህብረት እና የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የከፍተኛ ደረጃ ውይይት በሕብረቱ ዋና መቀመጫ ዛሬ በአዲስ አበባ ይደረጋል። በውይይቱ ላይ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ እንደሚገኙ ይጠበቃል። ውይይቱ በሁለቱ ወገኖች መካከል በአፍሪካ ልማት እና በዓለም አቀፍ አስተዳደር ዙሪያ ያለውን ስትራቴጂካዊ አጋርነት ማጠናከርን ያለመ ነው። በሁለቱ ድርጅቶች መካከል ያለውን ቅንጅት፣ የጋራ ተጠያቂነት እና ትብብርን በልማት፣ በአስተዳደር፣ በሰብአዊ ድጋፍ እና በሰላም ግንባታ ቅድሚያ በሚሰጣቸው ጉዳዮች ያላቸውን ትስስር ማሳደግ በሚቻልባቸው ጉዳዮች ላይ ውይይት ይካሄዳል። በዚህ የከፍተኛ ደረጃ ውይይት ላይ በርካታ ስትራቴጂካዊ ጉዳዮች የሚዳሰሱ ሲሆን፣ በተለይም የአጀንዳ 2063 እና የሁለተኛው የአስር ዓመት ምዕራፍ የትግበራ ዕቅድ አፈፃፀምን ማፋጠን እንዲሁም አፍሪካን በዓለም አቀፍ ፖሊሲ እና አስተዳደር ውስጥ ያላትን ማዕከላዊ ሚና መጠበቅ በሚሉ አጀንዳዎች ላይ ትኩረት ያደርጋል። በተጨማሪም "ከጥገኝነት ወደ ሉዓላዊነት" የተሸጋገረ የልማት ፋይናንስ፣ የ2026 የአፍሪካ ሕብረት የዓመቱ መሪ ቃል የሆነው ዘላቂ የውሃ አቅርቦት እና የንጽህና አጠባበቅ፣ እንዲሁም የዓለም አቀፍ ተቋማት ሪፎርም እና አፍሪካ በተባበሩት መንግሥታት የፀጥታው ምክር ቤት ያላትን ውክልና የተመለከቱ ጉዳዮች ውይይት ይደረግባቸዋል። መድረኩ ለአህጉራዊ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሔዎችን ማምጣት፣ የአገር ውስጥ ሀብት ማሰባሰብን ማሳደግ፣ የወጣቶች እና የሴቶች ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ እንዲሁም በአህጉራዊ እና በዓለም አቀፍ የልማት የቅድሚያ ትኩረቶች መካከል ያለውን ትስስር ማጠናከር ወሳኝ መሆኑ አጽንኦት የሚሰጥበት እንደሆነ ተመላክቷል። ከውይይቱ ከሚጠበቁ ውጤቶች መካከል የተሻለ ስትራቴጂካዊ ቅንጅት፣ ፍትሐዊ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ሥርዓት ለውጥ፣ በአፍሪካ ህብረት የዓመቱ መሪ ቃል ዙሪያ ጠንካራ ቅንጅት መፍጠር እና በተባበሩት መንግሥታት ሥርዓት ውስጥ ፍትሐዊ የአፍሪካ ውክልና እንዲኖር የቀረቡ ጥሪዎችን ማጠናከር እንደሚገኙበት ህብረቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ አመልክቷል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ የውይይቱን ውጤቶች አስመልክቶ የጋራ መግለጫ ይሰጣሉ።
የአህጉሪቷን የልማት ግቦች ለማሳካት የአፍሪካ ሕብረትና አባል ሀገራትን የፖሊሲ አቅጣጫ አሰናስሎ መምራት ይገባል 
Apr 28, 2026 2017
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦የአህጉሪቷን የልማት ግቦች ለማሳካት የአፍሪካ ሕብረትና አባል ሀገራትን የፖሊሲ አቅጣጫ አሰናስሎ መምራት እንደሚገባ የሕብረቱ ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊክ ሀዳዲ ገለጹ። በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከአፍሪካ ሕብረት፣ ከአፍሪካ ልማት ባንክና ሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበር "የአጀንዳ 2030 እና 2063 ግቦችን ለማሳካት የተቀናጀና አሻጋሪ አካሄድ መከተል" በሚል መሪ ሐሳብ ያዘጋጀው 12ኛው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን መካሄድ ጀምሯል። በየዓመቱ የሚካሄደው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ የአፍሪካ ሕብረትን የአጀንዳ 2030 እና 2063 የዘላቂ የልማት ግቦችን አፈፃጸም ይገመግማል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊክ ሀዳዲ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ አጀንዳ 2030 እና 2063 ጎን ለጎን የሚሄዱ ሳይሆን እርስ በርስ የሚደጋገፉ ናቸው።   የአፍሪካ ሕብረት የሁለተኛውን የአሥር ዓመት የአጀንዳ 2063 የትግበራ ዕቅድን ሀገር በቀል በማድረግ አካታች ዕድገትና ዘላቂ የኢኮኖሚ ሽግግርን የሚያፋጥን መሠረታዊ እርምጃ መውሰዱን ገልጸዋል። የሕብረቱ አባል ሀገራትም ብሔራዊ የልማት ዕቅዶችን ከአጀንዳው ጋር በማጣጣም የበጀት ድልድልና የፖሊሲ እርምጃዎችን ለአፍሪካ የትኩረት መስኮች ቅድሚያ እየሰጡ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህም አፍሪካ የአጀንዳ 2030 እና 2063 ዘላቂ የልማት ዕቅዶችን በመተግበር ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር እያሳየች መሆኑን ገልጸዋል። በአፍሪካ አጀንዳ 2030 እና 2063 ግቦች የበለጸገች አህጉርን እውን ለማድረግም የአባል ሀገራት ቅንጅትና ትብብር ቀጣይነት ሊኖረው ይገባል ብለዋል። የአጀንዳ 2030 የዘላቂ ልማት ግቦችን በማሳካት የተሳለጠ የለውጥ ሽግግርን ለመፍጠርም ጠንካራና የተሰናሰለ ሀገራዊ፣ ቀጣናዊና አህጉራዊ የፖሊሲ ፍሰት ሊኖር እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ለዚህም የመንግሥታት፣ የግሉ ዘርፍና የልማት አጋሮች በወሳኝ የኢንቨስትመንት ዘርፎች ላይ የሚኖራቸውን ትብብርና ቅንጅት የሚያበረታታ ምኅዳር መፍጠር እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል።   የዑጋንዳ ጠቅላይ ሚኒስትርና ተሰናባቿ የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ ቢሮ ሊቀ-መንበር ሮቢናህ ናባንጃ በበኩላቸው፤ የአፍሪካውያን ድምፅ በወሳኝ የዓለም መድረኮች ላይ መንፀባረቅ እንዳለበት ገልጸዋል፡፡ አፍሪካውያን በዓለም አቀፍ መድረኮች በከፍተኛ ደረጃ ከሚደረግ ፖለቲካዊ ተሳትፎ ባለፈ በወሳኝ ስትራቴጂክ ሂደቶች ላይ በንቃት መሳተፍ ይገባቸዋል ብለዋል። የአፍሪካ ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካትም ሎጂስቲክስ፣ ትራንስፖርትና መሰል የትኩረት ዘርፎች ላይ በስፋት በመሰማራት ቀጣናዊ ትስስርን ማጠናከር እንደሚገባ ተናግረዋል።
አፍሪካ የአጀንዳ 2030 እና 2063 ዘላቂ የልማት ዕቅዶችን በመተግበር ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር እያሳየች ነው
Apr 28, 2026 1417
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2018(ኢዜአ)፦ አፍሪካ የአጀንዳ 2030 እና 2063 ዘላቂ የልማት ዕቅዶችን በመተግበር ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር እያሳየች መሆኑን የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊክ ሀዳዲ ገለጹ። በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከአፍሪካ ሕብረት፣ ከአፍሪካ ልማት ባንክና ሌሎች አጋር አካላት ጋር በመተባበር "የአጀንዳ 2030 እና 2063 ግቦችን ለማሳካት የተቀናጀና አሻጋሪ አካሄድ መከተል" በሚል መሪ ሐሳብ ያዘጋጀው 12ኛው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ በአዲስ አበባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን መካሄድ ጀምሯል። በየዓመቱ የሚካሄደው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ጉባኤ የአፍሪካ ሕብረትን የአጀንዳ 2030 እና 2063 የዘላቂ የልማት ግቦችን አፈፃፀም ይገመግማል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ-መንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊክ ሀዳዲ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ አጀንዳ 2030 እና 2063 በትይዩ የሚሄዱ ሳይሆን እርስ በርስ የሚደጋገፉ ናቸው። በአፍሪካ አካታች ዕድገትና ዘላቂነት ያለው የኢኮኖሚ ሽግግር ለመፍጠር ወሳኝ መሆናቸውንም ገልጸዋል። የአፍሪካ ሕብረት የሁለተኛውን የአሥር ዓመት የአጀንዳ 2063 የትግበራ ዕቅድ ሀገር በቀል እንዲሆን መሠረታዊ እርምጃ መውሰዱን ተናግረዋል። የሕብረቱ አባል ሀገራት ብሔራዊ የልማት ዕቅዶቻቸው ከአጀንዳው ጋር እየተጣጣመ መምጣቱን በማንሳት፤ የበጀት ድልድልና ፖሊሲዎቻቸው ለአፍሪካ የትኩረት መስኮች ቅድሚያ የሰጡ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የአጀንዳ 2030 እና 2063 ግቦችን በማሳካት የበለጸገች አፍሪካን እውን ለማድረግ በሀገራት መካከል ያለው ቅንጅትና ትብብር ቀጣይነት ሊኖረው እንደሚገባም አስገንዝበዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ #ENA
አፍሪካውያን የአረንጓዴ ኢንዱስትሪ አብዮትና ዘላቂ ልማት ግቦችን ለማሳካት የማዕድን ሀብታቸውን እሴት በመጨመር ለዓለም ገበያ ማቅረብ አለባቸው
Apr 27, 2026 1310
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2018 (ኢዜአ)፦‎ አፍሪካውያን የአረንጓዴ ኢንዱስትሪ አብዮትና ዘላቂ ልማት ግቦችን ለማሳካት የማዕድን ሀብታቸው ላይ እሴት በመጨመር ለዓለም ገበያ ማቅረብ እንዳለባቸው የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሀፊ ክላቨር ጋቴቴ ገለጹ፡፡ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ከታንዛኒያ የአፍሪካ ዘላቂ ልማት አመራር ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "የአፍሪካ ወሳኝ ማዕድናትን ለአረንጓዴ የኢንዱስትሪ አብዮትና ዘላቂ ልማት ማዋል" በሚል መሪ ሃሳብ ያዘጋጁት የ12ኛው የአፍሪካ ዘላቂ ልማት ቀጣናዊ ቅድመ ጉባኤ ተካሂዷል፡፡ የተባበሩት መንግሥታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ጸሀፊ ክላቨር ጋቴቴ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ አፍሪካ እንደ ኮባልት፣ ሊቲየም፣ ግራናይት እና ሌሎች የከርሰ ምድር ሀብቶችን ጨምሮ የዓለምን 30 በመቶ ማዕድናትን ይዛለች፡፡ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ብቻዋን የዓለምን ከፍተኛ የኮባልት ማዕድን የያዘች መሆኑን ገልጸው፤ ይሄውም አፍሪካን የዓለም አቀፍ የኃይል ሽግግር /Energy Transition/ ማዕከል ያደርጋታል ብለዋል፡፡ አፍሪካ ዩራኒዬምና ሌሎች የከርሰ ምድር የከበሩ ማዕድናት ባለቤት መሆኗን በመጥቀስ፤ ለዓለም አቀፉ የኒውክሌር ኃይል አቅርቦት አስተዋጽኦ ከማድረግ ባለፈ ብዙ የአፍሪካ ሀገራት ወደ ኒውክሌር ኃይል ልማት እያመሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ አፍሪካ የከበሩ ማዕድናት ባለቤት ብትሆንም አብዛኛው በጥሬ እቃ መልክ ወደ ውጭ የሚላክ በመሆኑ የአህጉሪቱ የእርስ በእርስ ግብይት ከሁለት በመቶ እንዳማይዘል ተናግረዋል፡፡ በአህጉሪቱ የማዕድናት ማምረቻና ማቀነባበሪያ ፋብሪካዎችን መገንባት ቢቻል በየዓመቱ ከ24 ቢሊየን ዶላር በላይ ተጨማሪ ገቢ ማግኘትና ለ2 ነጥብ 3 ሚሊየን ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ይቻላል ብለዋል፡፡ የአፍሪካ የማዕድን ፖሊሲ ለእሴት መጨመር፣ ኢንዱስትሪ ልማትና ሁሉን አቀፍ ልማት ቅድሚያ የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም በአህጉሪቱ የተቀናጀ ቀጣናዊ ኢንዱስትሪ ለመገንባት ያለውን ፍላጎት በአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ማዕቀፍ አህጉራዊ የማዕድን ሀብቶችን ወደ ዘላቂ ብልጽግና መለወጥ ይገባል ብለዋል፡፡ በዚህም የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ቀጣናዊ እሴት ሰንሰለትን በማጠናከር የማዕድን ጸጋዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል በሚደረገው ጥረት ትብብሩን ማጠናከሩን እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡ የአፍሪካ ዘላቂ ልማት አመራር ኢንስቲትዩት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ካዳሪ ሲንጎ በአፍሪካ ሁሉን አቀፍና አካታች ዕድገት ለማስመዝገብ የማዕድን ሀብቶችን በአግባቡ ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ አፍሪካውያን በተፈጥሮ ሀብታችን ላይ የሚኖረን ትብብርና ተሳትፎ ስትራቴጂያዊና መዳረሻ ግብ ያለው መሆን እንዳለበት ገልጸዋል፡፡ በአፍሪካ ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥና የአረንጓዴ ኢንዱስትሪ አብዮት ሽግግርን ለመፈጠር በአቅም ግንባታ ድጋፍ እናደርጋለን ብለዋል፡፡
አምባሳደር ቆንጂት ስነጊዮርጊስ የአፍሪካ ዲፕሎማሲ እሴቶች ተምሳሌት ነበሩ
Apr 7, 2026 1841
አዲስ አበባ፤መጋቢት 29/2018 (ኢዜአ)፦አምባሳደር ቆንጂት ስነጊዮርጊስ የአፍሪካ ዲፕሎማሲ ከፍተኛ እሴት በተግባር ያሳዩ ታላቅ ዲፕሎማት ነበሩ ሲሉ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። ሊቀመንበሩ በኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ታሪክ ውስጥ ስመጥር በሆኑት አምባሳደር ቆንጂት ስነጊዮርጊስ ህልፈት የተሰማቸውን ጥልቅ ሀዘን ገልጸዋል። ሊቀመንበሩ አምባሳደሯን የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት አገልግሎት ፈር ቀዳጅ፣ ታላቅ ዲፕሎማት እና ህይወታቸውን ለሀገራቸውና ለአህጉሪቱ እድገት የሰጡ ጽኑ አፍሪካዊት ሲሉ አወድሰዋቸዋል። አምባሳደር ቆንጂት ስነጊዮርጊስ ለበርካታ አስርተ አመታት የዘለቀ አርአያነት ያለው ሙያዊ ስኬት ማስመዝገባቸውንና ከኢትዮጵያ ቀዳሚ ሴት አምባሳደሮች አንዷ በመሆንም ለአፍሪካውያን ሴት ዲፕሎማቶች የብርሃን ፋና መሆናቸውን አመልክተዋል። የአፍሪካን ጥቅም ለማስከበርና ዓለም አቀፍ ትብብርን ለማጠናከር የነበራቸው የማይናወጥ ቁርጠኝነት ለአህጉራዊ የጋራ ግቦች መሳካት የጎላ ሚና እንደነበረውም አውስተዋል። ሊቀመንበሩ አምባሳደር ቆንጂት በታማኝነት፣ በልዩ ብቃት እና ለጋራ የወደፊት እጣ ፈንታ የነበራቸው ጽኑ ቁርጠኝነት የአፍሪካ ዲፕሎማሲ እሴቶች ያላቸውን ጽኑ አቋም ያሳየ መሆኑንም ነው ያነሱት። የአምባሳደሯ የዲፕሎማሲ አሻራ ለቀጣይ ትውልድ ዲፕሎማቶች፣በተለይም ለሴቶች፣በድፍረትና በዓላማ እንዲያገለግሉ ዘላቂ መነሳሳት ሆኖ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል። ሊቀመንበሩ በአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ስም ለአምባሳደር ቆንጂት ቤተሰቦች፣ ለኢትዮጵያ መንግስትና ህዝብ፣ እንዲሁም ለሁሉም አፍሪካውያን ልባዊ መጽናናትን ተመኝተዋል።
ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት የሰላምና የፀጥታ ምክር ቤት ሊቀ መንበርነትን ተረከበች
Apr 3, 2026 1104
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 25/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የእ.አ.አ አፕሪል 2026 የአፍሪካ ህብረት የሰላም እና ፀጥታ ምክር ቤት (AU PSC) ተዘዋዋሪ ሊቀመንበርነትን በይፋ መረከቧን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል። ኢትዮጵያ ሊቀ መንበርነቱን የተረከበችው ከኮትዲቯር ነው። ኢትዮጵያ መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም የምክር ቤቱን አጀንዳዎች በሊቀመንበርነት መምራት እንደምትጀምር ሚኒስቴሩ አመልክቷል። በዚህም ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2025 በድጋሚ የምክር ቤቱ አባል ሆና ከተመረጠች በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ሊቀ መንበር መሆን ችላለች። በሊቀመንበርነት ቆይታዋ ኢትዮጵያ በአህጉሪቱ በሚገኙ አገራዊ እና ወቅታዊ የሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ላይ የሚደረጉ ውይይቶችን እንደምትመራ ሚኒስቴሩ አስታውቋል። የኢትዮጵያን ሊቀ መንበርነት በይፋ ለማብሰር እና አዲስ የተመረጡ የምክር ቤቱን አባላት ለመቀበል መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም በኢትዮጵያ ሰብሳቢነት የሰንደቅ ዓላማ የማውለብለብ ሥነ-ሥርዓት ይከናወናል። ኢትዮጵያ እ.ኤ.አ. በ2004 ምክር ቤቱ ከተመሰረተ ጀምሮ በአባልነት ስታገለግል የቆየች መሆኑን የጠቀሰው የሚኒስቴሩ መግለጫ፤ እ.አ.አ በ2025 በድጋሚ ለሦስት ዓመታት አባል ሆና መመረጧን አውስቷል። ኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም አራት ጊዜ የምክር ቤት አባል ሆና ተመርጣ በንቃት ስትሳተፍ መቆየቷ ተወስቷል።
ድርጅቱ የብዙኃነት አቅም ያለው በመሆኑ ይህን አቅም ወደ ስትራቴጂያዊ ጥቅም ማምጣት ያስፈልጋል
Mar 28, 2026 1316
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 19/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ፣ ካርቢያን እና ፓስፊክ ሀገራት ድርጅት የብዙኃነት አቅም ያለው በመሆኑ ይህን አቅም ወደ ስትራቴጂያዊ ጥቅም ማምጣት እንደሚያስፈልግ የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ አስገነዘቡ። 11ኛው የአፍሪካ፣ ካርቢያን እና ፓስፊክ ሀገራት ድርጅት የመሪዎች ጉባኤ በማላቡ ኢኳቶሪያል ጊኒ እየተካሄደ ይገኛል። በጉባኤው እየተሳተፋ የሚገኙት የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ ድርጅቱ የብዙኃነት አቅም ያለው በመሆኑ ይህን አቅም ወደ ስትራቴጂያዊ ጥቅም ማምጣት ያስፈልጋል ብለዋል። ተለዋዋጭ በሆነው የአለም የኢኮኖሚ እና ፖለቲካ ውስጥ የአባል ሀገራቱን ጥቅም የሚያስከብር ጠንካራ ድርጅት ሆኖ መቀጠል እንዳለበትም በአፅንኦት ተናግረዋል። ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ በንግግራቸው ለድርጅቱ ጥንካሬ ይበጃሉ ያላቸውን ሀሳቦችም አካፍለዋል። በዚህም ድርጅቱ የብዙኃነት አቅም ያለው በመሆኑ ይህን አቅም ወደ ስትራቴጂያዊ ጥቅም ማምጣት ያስፈልጋል ነው ያሉት።   ለዚህም የደቡብ - ደቡብ ግንኙነትን ማጠናከር ቁልፍ ሚና ይኖረዋል ያሉ ሲሆን መካከለኛ እና ከፍተኛ ኢኮኖሚን ከገነቡ ሀገራትና ድርጅቶች ጋር ያለን ግንኙነት ከቀደመው የእርዳታ ሰጭ እና ተቀባይ ግንኙነት ወደ የጋራ ተጠቃሚነት ለማሸጋገር መስራት ያስፈልጋል ብለዋል። የድርጅቱ አባል ሀገራት ተመሳሳይ የባለቤትነት ስሜትን ማዳበር እንዳለባቸውም ፕሬዚዳንቱ ጠቁመዋል። ቀጣይነት ያለው ልማት ማረጋገጥ፣ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ መገንባትና ሰላምና ፀጥታን ለማስፈን መስራት የአባል ሀገራት የጋራ የትኩረት አቅጣጫዎች መሆን እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። የአፍሪካ፣ ካርቢያን እና ፓስፊክ ሀገራት ድርጅት አባል ሀገራት ዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ ያላቸው ሚና ከተጠቃሚነት ወደ ፈጣሪነት(አምራችነት) መሸጋገር እንዳለበትም ተናግረዋል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ ሳይበር ደህንነት እና የዲጂታል ቴክኖሎጂ ሉዓላዊነት ጉዳይ በልዩ ትኩረት ሊሰራባቸው እንደሚገባም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ኢኮኖሚ በመገንባት ረገድ ባስመዘገበቻቸው ውጤቶች ቀጣዩን የአለም የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤን (ኮፕ 32) እንድታስተናግድ መመርጧን አስታውሰዋል። ይህም የአፍሪካ፣ ካርቢያን እና ፓስፊክ ሀገራት ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አረንጓዴ ልማት በመገንባት ሂደት ያላቸውን ተሞክሮ የሚያቀርቡበት ትልቅ ዕድል እንደሆነም ፕሬዚዳንቱ አስረድተዋል።   የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሀፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በበኩላቸው ሶስቱም ቀጣናዎች የጎላ አስተዋጽኦ ባላደረጉበት የአየር ንብረት ለውጥ ከፍተኛ ጉዳት እያስተናገዱ መሆናቸውን አንስተዋል። የአየር ንብረት ፍትህ እንዲረጋገጥ የተባበረ እንቅስቃሴ እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል። በጉባኤው አፍሪካ፣ ካርቢያን እና ፓስፊክ ክልሎችን የወከሉ መሪዎች ንግግር ያደረጉ ሲሆን አፍሪካን በመወከል የወቅቱ የአፍሪካ ኅብረት ሊቀመንበር እና የቡሩንዲ ፕሬዚዳንት ኤቫሪስት ንድዪሺሚዬ መልእከት አስተላልፈዋል። የድርጅቱን የፋይናንስ ምንጭ ቀጣይነት ማረጋገጥ፣ የድርጅቱን መዋቅራዊ አሰራር ማጠናከር እንዲሁም በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የጋራ አቋም መያዝ በጉባኤው ጎልተው የተሰሙ ድምፆች መሆናቸውን ኢዜአ ከስፍራው ዘግቧል። በማላቡ ኢኳቶሪያል ጊኒ እየተካሄደ የሚገኘው 11ኛው የአፍሪካ፣ ካርቢያን እና ፓስፊክ ሀገራት ድርጅት የመሪዎች ጉባኤ እስከ ነገ መጋቢት 20/2018 ዓም ድረስ ይቆያል። በጉባኤው ከሶስቱም ክልሎች የሚገኙ የሀገራት መሪዎች እንዲሁም የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፣ የአፍሪካ ህብረት እና የአውሮፓ ህብረት ተወካዮች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
የዓለም የውሃ ቀን እየተከበረ ነው 
Mar 22, 2026 1031
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 13/2018 (ኢዜአ)፦ 34ኛው የዓለም የውሃ ቀን ዛሬ በዓለም ደረጃ እየተከበረ ይገኛል። “ውሃ እና ስርዓተ ጾታ” የዘንድሮ መሪ ቃል ነው። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የውሃ ቀን ቁልፍ መልዕክቶችን ይፋ አድርጓል። ተመድ የዓለም የውሃ ቀውስ ለሁሉም ሰው የሚተርፍ ቢሆንም ተፅዕኖው ግን እኩል እንዳልሆነ አመልክቷል። ሰዎች ደህንነቱ የተጠበቀ የመጠጥ ውሃ እና የንጽሕና መጠበቂያ አገልግሎቶችን የማግኘት ሰብአዊ መብታቸው በማይከበርባቸው ቦታዎች ላይ ኢ-ፍትሃዊነት ጎልቶ እንደሚታይ ገልጿል። በዚህም ሴቶችና ልጃገረዶች የችግሩ ዋነኛ ሰለባ እንደሚሆኑ ጠቅሶ ሴቶችና ልጃገረዶች የውሃ መፍትሔዎች ማዕከል የምናደርግበት ጊዜ አሁን ነው ብሏል። ሴቶች የውሃን የወደፊት ዕጣ ፈንታ መቅረጽ አለባቸው ያለው ተመድ ለዚህም የሴቶች ድምፅ፣ አመራር እና ተሳትፎ ማሳደግ እንደሚገባ ነው ያስታወቀው። በዘንድሮው የዓለም ውሃ ቀን ከሚተላለፉ መልዕክቶች አንዱ ውሃ ባለበት እኩልነት ያብባል የሚለው እሳቤ ነው። ሴቶችና ልጃገረዶች በውሃ ውሳኔዎች ላይ እኩል ድምፅ ሲኖራቸው፣ አገልግሎቶቹ ይበልጥ አካታች፣ ቀጣይነት ያላቸው እና ውጤታማ እንደሚሆኑ ተመድ አመልክቷል። ለሁሉም የሚተርፍ ጤናማ፣ የበለጸገ እና እኩልነት የሰፈነበት መጻኢ ጊዜን ለመገንባት፤ የሴቶች የውሃ ዘርፍ አመራር ሰጪነት ለማሳደግ የሚያስችል ስራን ማከናወን እንደሚገባም አስታውቋል። የዓለም የውሃ ቀን ከእ.አ.አ 1993 ጀምሮ እየተከበረ ይገኛል። እ.አ.አ 1992 በብራዚል ሪዮ ዴጄኔሮ በተካሄደው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የከባቢ አየር እና ልማት ኮንፍረንስ (ሪዮ ኮንፍረንስ) የዓለም መሪዎች የውሃ ሀብቶችን መጠበቅ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አንስተዋል። ከኮንፈረንሱ ውጤቶች መካከል አንዱ ውሃን አስመልክቶ ግንዛቤ መፍጠር ላይ ያተኮረ ቀን የመሰየም ምክረ ሀሳብ ነው። በዚሁ መሰረት ተመድ እ.አ.አ 1992 ባደረገው ጠቅላላ ጉባኤ በዓለም አቀፍ ደረጃ በማርች 22 እንዲከበር ውሳኔ አስተላልፏል። ውሳኔውን ተከትሎ የዓለም የውሃ ቀን ከእ.አ.አ 1993 ጀምሮ እየተከበረ ይገኛል። በዓለም በላይ ከሁለት ቢሊዮን በላይ ሰዎች ደህንነቱ የተጠበቀ የመጠጥ ውሃ እንደማያገኙ መረጃዎች ያመላክታሉ። የአየር ንብረት ለውጥ እና ፈጣን የህዝብ እድገት ለውሃ እጥረት ዋንኛ መንስኤዎች ናቸው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም