ዓለም አቀፍ ዜናዎች - ኢዜአ አማርኛ
ዓለም አቀፍ ዜናዎች
መካከለኛ ገቢ ያላቸው የአፍሪካ ሃገራት በሰው ሃብት ልማት ላይ ትኩረት ሊያደርጉ እንደሚገባ ተገለጸ
Dec 7, 2023 78
አዲስ አበባ ፤ ህዳር27/2016(ኢዜአ)፡- መካከለኛ ገቢ ያላቸው የአፍሪካ ሃገራት ፈጠራን ማእከል ያደረገ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት እንዲያመጡ በሰው ሃብት ልማት ላይ አተኩረው ሊሰሩ እንደሚገባ ተመለከተ። በአፍሪካ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ሃገራት በሚያጋጥሟቸው ተግዳሮቶች ዙሪያ በፖሊሲ አውጭዎች፣ በምሁራን እና የልማት አጋሮች እና በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን ትብብር በተዘጋጀው የበይነመረብ የውይይት መርሃግብር ላይ እንደተገለጸው የሰለጠነ ሰው ሃብት አቅም በሚፈለገው ደረጃ አለመገኘት እና የመንግስት እዳ መጨመር መካከለኛ ገቢ ያላቸው የአፍሪካ ሃገራት ዋነኛ ተግዳሮቶች ናቸው ተብሏል። በተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን የሰሜን አፍሪካ ዳይሬክተር ዙዛና ብሪክሾቫ ሽዊድሮዊስኪ “ ሃገራት በሰው ሃብት ክህሎት ላይ በትኩረት መስራትና የትምህርት ስርአታቸውን ከጊዜው ጋር ማራመድ አለባቸው” ያሉ ሲሆን “ከአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች ጋር ተዋውቆ ምን፣ እንዴት፣ የትና መቼ መስራት እንዳለበት የተገነዘበ ዜጋ የሚፈጥሩ ከሆነ ካሉበት ማነቆ ፈጥነው መውጣት ይችላሉ” ሲሉ መክረዋል። ወቅቱ የሚጠይቀውን የሰለጠነ የሰው ሃይል ማቅረብ ያልቻሉት የአፍሪካ ባለ መካከለኛ ገቢ ሃገራት ፈጠራን ማእከል ያደረገ እድገት ለማምጣት እየተቸገሩ መሆኑን ይፋ ያደረገው የተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን ሃገራቱ የሚፈለገውን ለውጥ እንዲያስመዘግቡም የሰው ሃብታቸው ላይ ከወዲሁ መስራት አማራጭ የማይገኝለት መፍትሄ ነው ብሏል። አራተኛውን የኢንዱስትሪ አብዮት ተቀላቅሎ ባለከፍተኛ ገቢ የመሆን ርእይ ያላቸው ሃገራት መዋቅራዊ ሽግግራቸውን በዘላቂነት ለማሳካት ያግዙናል የሚሏቸውን አዳዲስ ፈጠራዎችና ወቅቱ የሚሰጣቸውን እድሎች አሟጠው መጠቀም እንዳለባቸውም ኮሚሽኑ መክሯል። ከሌሎች ሃገራት አንጻር እነዚህ ሃገራት መንግስታዊ የእዳ ጫናቸው እያደገ በመምጣቱ ዘላቂ እድገትና ልማት ማስመዝገብ ብሎም ዘላቂ የልማት ግቦችን በማሳካት የዜጎቻቸውን ህይወት በአስተማማኝ ሁኔታ የመቀየር ጥረታቸው እየተገደበ መሆኑን ያተተው ዘገባው ሃገራቱ አሁን ባለው የገንዘብ ስርአት እምነት እንዲያጡ እያደረጋቸው መሆኑንም አንስቷል። በዚህ ጉዳይ ላይ ምሁራን ተመራማሪዎች ፖሊሲ አውጭዎች እና የልማት ባለድርሻዎችን በማካተት ሰፋ ያለ የምክክር ጉባኤ በሞሮኮዋ ማራካሽ ለማድረግ ለሚመጣው የካቲት ቀጠሮ መያዙንም የዥንዋ ዘገባ አመልክቷል፡፡
የኢትዮጵያ ብሪክስን መቀላቀል ከሩሲያ ጋር ያላትን ትብብር ያጠናክራል - ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን
Dec 5, 2023 217
አዲስ አበባ፤ ህዳር 25/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ ብሪክስን መቀላቀሏ ከሩሲያ ጋር ያላትን ትብብር የበለጠ የሚያጠናክረው መሆኑን የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን ገለጹ። በሩሲያ ፌዴሬሽን የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ቻም ኡጋላ ኡሪያት የሹመት ደብዳቤያቸውን ለሩሲያው ፕሬዝዳንት አቀርበዋል ፡፡ አምባሳደሩ የሹመት ደብዳቤያቸውን ባቀረቡበት ወቅት ፕሬዝዳንት ፑቲን ባስተላለፉት መልዕክት ኢትዮጵያና ሩሲያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከመሰረቱ 125 ዓመታትን ያስቆጠሩ ወዳጅ አገራት መሆናቸውን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ በቅርቡ በሩሲያ ይፋዊ የስራ ጉብኝት በማድረግ የተለያዩ የትብብር ስምምነቶች መፈረማቸው ግንኙነቱን ከፍ ወዳለ ደረጃ እንዳሻገረው መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል። ኢትዮጵያ ብሪክስን መቀላቀሏ ደግሞ የሁለቱን ሃገራት ግንኙነት የበለጠ እንደሚያጠናክረው ተናግረዋል፡፡
በታንዛንያ በተከሰተ የመሬት መንሸራተት የ47 ሰዎች ህይወት ማለፉ ተገለጸ
Dec 4, 2023 121
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 24/2016 (ኢዜአ) ፦ በታንዛንያ ከባድ ዝናብ መጣሉን ተከትሎ በተከሰተ የመሬት መንሸራተት በትንሹ የ47 ሰዎች ህይወት ማለፉ ተገልጿል። የአየር ንብረት ለውጥን ተከትሎ ከፓስፊክ ውቅያኖስ የሚነሳው ዝናብ አዘሉ የአሌ ኒኖ ክስተት ታንዛንያን ጨምሮ በኬኒያና በሶማልያ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ይገኛል። በሰሜን ታንዛንያም ከቅዳሜ ጀምሮ እየጣለ የሚገኘው ነፋስ የቀላቀለ ዝናብ ባስከተለው የመሬት መንሸራተት አደጋ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሱን ዘጋርዲያን በዘገባው አስነብቧል። በሰሜናዊ ታንዛንያ ካቴሽ ከተማ በተከሰተው አደጋ እስከ ትላንት ምሽት ድረስ በተንሹ የ47 ሰዎች ህይወት ማለፉንና 85 ሰዎች መጎዳታቸውን ተጠቅሷል። በግዛቲቱ እየጣለ የሚገኘውን ነፋስ የቀላቀለ ዝናብ ተከትሎ የተጎጂዎች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ያመለከተው ዘገባው ለአካባቢው ነዋሪዎች የማስጠንቀቂያ መልዕክት ከግዛቲቱ የአደጋ መከላከል ኮሚሽን መተላለፉንም ገልጿል።
የአየር ንብረት ለውጥ ቀውስ ከ 12 ሆስፒታሎች አንዱን የመዝጋት አደጋን ደቅኗል
Dec 4, 2023 122
አዲስ አበባ፤ ህዳር 24/2016 (ኢዜአ)፦የካርበን ልቀትን መቆጣጠር ካልተቻለ በአለማችን ካሉ 12 ሆስፒታሎች አንዱ በአየር ንብረት ቀውስ ሙሉ በሙሉ አለያም በከፊል የመዘጋት አደጋ መደቀኑን ጥናት አመለከተ። ይህ ጥናት የቀረበው በዱባዩ ኮፕ28 የመሪዎች የጤና ጉባኤ ላይ ነው። የካርበን ልቀትን መቆጣጠር ካልተቻለ በሚያስከትለው የአየር ንብረት ቀውስ በአለማችን ካሉ 12 ሆስፒታሎች አንዱ ሙሉ በሙሉ አለያም በከፊል የመዘጋት አደጋ አንደተደቀነበት የሲተቪ ኒውስ ዘገባ ያመለክታል። በክሮስ ዲፔንዳንሲ ኢኒሼቲቭ የሳይንስና ቴክኖሎሊ ዳይሬክተር ዶክተር ካረለ ማሎን በኮፕ 28 ዱባይ የጤና ጉባኤ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት እንዳመለከቱት ለጥናት ከተወሰዱ ከ200ሺ 216 ሆስፒታል ናሙናዎች ከ12 አንዱ አደጋላይ ነው ። የአየር ንብረት ለውጡ ሆስፒታሎች ላይ የሚያስከትለው አውሎ ንፋስ፣ የጎርፍ መጥለቅለቅ ወይም የደን ቃጠሎ ስራቸውን ያስተጓጉላል አለያም ወደ ሌላ ቦታ እንዲቀይሩ ያስገድዳቸዋል እንደ ሪፖርቱ ገለጻ። ችግሩን መቅረፍ ካልተቻለም በምእተአመቱ መገባደጃ የአለማችን 16ሺ245 ሆስፒታሎች በአየር ንብረት ለውጡ ሙሉ በሙሉ አለያም በከፊል ይዘጋሉ ። የአየር ንብረት ለውጥ በጤና ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ለመቀነስም የቅሪተ አካላት ነዳጅ አጠቃቀምን መቆጣጠር አስገዳጅ ነው።
የታዳሽ ሃይል አቅርቦትን በሶስት እጥፍ ለማሳደግ ለቀረበው ጥሪ የበርካታ አገራት ድጋፍ አገኘ
Dec 3, 2023 111
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ)፦ የታዳሽ ሃይል አቅርቦትን በሶስት እጥፍ ለማሳደግ ለቀረበው ጥሪ የበርካታ አገራት ድጋፍ ማግኘቱ ተገለጸ። በዱባይ እየተካሄደ ባለው የዓለም የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ላይ እየተሳተፉ የሚገኙት የአገራት መሪዎች የታዳሽ ሃይል አቅርቦትን በዓለም አቀፍ ደረጃ በሶስት እጥፍ ለማሳደግ መስማማታቸውን ተዘግቧል። ከአንድ መቶ አስር በላይ የሚሆኑ የአገራት መሪዎች እንደአውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2030 የታዳሽ ሃይል አቅርቦትን በሶስት እጥፍ ለማሳደግ ለቀረበው ጥሪ አዎንታዊ ምላሽ መስጠታቸውን የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዝደንት ኡርሱላ ቮንደር ሊይን ገልጸዋል። መንግስታትም ሆኑ ግዙፍ ኩባንያዎች ከፍ ያለ መዋእለ ንዋያቸውን ለዚሁ አላማ መሳካት ያውላሉ ወይ የሚለው ጥያቄ መመለስ እንደሚኖርበት አጽንኦት የሰጡት ፕሬዝደንቷ የግብአት አቅርቦት፣ የዋጋ ጭማሪ፣ በዘርፉ የሰለጠነ የሰው ሃይል እንዲሁም የፕሮጀክቶች አፈጻጸምን የተመለከቱ ጉዳዮች ከውሳኔው በኋላ መፍትሄ የሚፈለግላቸው ይሆናል ብለዋል። በጉባኤው የሚነሳው ሃሳብ የሁለት መቶ አገራት ይሁንታ የሚፈልግ መሆኑን የተነገረ ሲሆን የአውሮፓ ህብረት፣ አሜሪካና ዩናይትድ አረብ ኤምሬት ጥሪውን በግንባር ቀደምነት የተቀበሉ ናቸው። ቻይናና ህንድ በይፋ ሃሳባቸውን ባይገልጹም በካይ የሚባሉትን የድንጋይ ከሰልና የነዳጅ ዘይት የሃይል ምንጮችን በመቀነስ የታዳሽ የኃይል አማራጮችን በ2030 በሶስት እጥፍ ማሳደግ በሚለው ሃሳብ ዙሪያ የመስማማት አዝማሚያ ማሳየታቸውን ተገልጿል። ደቡብ አፍሪካ፣ ቪየትናም፣ አውስትራሊያ፣ ጃፓን፣ ካናዳ፣ ቺሊና ባርባዶስ ሃሳቡን በይፋ መቀበላቸውን ከገለጹ አገራት መካከል ተጠቃሽ መሆናቸውን የኢነርጂ ዎርልድ ዘገባ ያመለክታል።
የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች ለአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖ መፍትሄዎች 30 ቢሊየን ዶላር ለመስጠት ቃል ገባች
Dec 1, 2023 193
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 21/2016 (ኢዜአ)፡- የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች ለአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖ መፍትሄዎች ለሚደረገው ጥረት 30 ቢሊየን ዶላር ለመስጠት ቃል ገብታለች። የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች ፕሬዝዳንት ሼህ መሀመድ ቢን ዛይድ አል ናሕያን የኮፕ 28 ጉባኤን በከፈቱበት ወቅት በዓለም አቀፍ ደረጃ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን ለመዋጋትና ለችግሩ መፍትሄ ለመስጠት የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ ሀገራቸው 30 ቢሊየን ዶላር እንደምትለግስ ቃል ገብተዋል። ገንዘቡ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በሚደረገው ጥረት የሚያጋጥመውን የፋይናንስ ክፍተት ለመሙላትና ለማጠናከር እንደሚውል ተናግረዋል። ሼክ መሀመድ ቢን ዛይድ በንጹህ ሃይል ዘርፍ ላይ መዋዕለ-ነዋይን ለማፍሰስና የንጹህ ሃይል ሽግግር ለማድረግ በቂ የሆነ የፋይናንስ አቅርቦት እንቅፋት ሆኖ መቆየቱን ገልጸዋል። ኮፕ28 ለአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖ መፍትሄዎች ሀገራት እንዲተባበሩ፣ አንዲወያዩና ውሳኔዎችን እንዲያሳልፉ በማሰብ የተዘጋጀ ጉባኤ ነው ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተጽእኖዎችን ለመዋጋት የተባበሩት ዓረብ ኢምሬቶች በርካታ ስራዎችን መስራቷን ጠቅሰው፤ በተለይ የካርበን ልቀት መጠንን እ.አ.አ በ2030 በ40 በመቶ ለመቀነስና በ2050 ደግሞ ዜሮ ለማድረስ የተደረሰውን ስምምነት ለማሳካት በንጹህ ሃይል ዘርፍ ላይ መዋዕለ ነዋይ እያፈሰሰች እንደምትገኝ ገልጸዋል። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዓመታዊ የአየር ንብረት ጉባኤ በዱባይ እየተካሄደ ሲሆን የሀገራት መሪዎች የአየር ንብረት ለውጥ በተለይ በማደግ ላይ ባሉ ሀገራት ላይ እያደረሰ የሚገኘውን ተጽእኖ ለመዋጋት የሚጠበቅባቸውን ፈንድ ለመመደብ ቃል ይገባሉ ትብሎ ይጠበቃል።
በአየር ንብረት መዛባት ምክንያት የሰው ልጆች ህልውና አደጋ ላይ ናቸው- ተመድ
Dec 1, 2023 113
አዲስ አበባ፤ ህዳር 21/2016 (ኢዜአ)፦ የአየር ንብረት መዛባት በሰው ልጆች ህልውና ላይ አደጋ የደቀነ መሆኑን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አስገነዘበ። የድርጅቱ ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ዱባይ እየተካሄደ ባለው ኮፕ 28 የአየር ንብረት ጉባኤ ላይ ተገኝተው ባደረጉት ንግግር አሁን ላይ የአየር ንብረት ለውጥ ለሰው ልጆች ህልውና አሳሳቢ እየሆነ መምጣቱን ተናግረዋል። በዱባይ እየተደረገ ባለው የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ የሃገራት መሪዎች ችግሩን ለመከላከል የሚያስችል ተግባራዊና ተስፋ ሰጪ እርምጃዎች እንዲወሰዱ ዋና ጸሃፊው ጥሪ አቅርበዋል። የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል የተሻለ ዓለም ለመፍጠር “በአመራር ብቃት፣ በአለምአቀፍ ትብብር እና በፖለቲካ ቁርጠኝነት ተግባራዊ እርምጃ እንውሰድ” ሲሉ ጥሪ ያቀረቡት ዋና ጸሃፊው፤ ከአመታት በፊት መከናወን የነበረባቸው በርካታ ውዝፍ ስራዎች አሉ ብለዋል። በማደግ ላይ ያሉ ሃገራት ባልፈጠሩት ችግር ጉዳት እያስተናገዱ እንደሆነ የገለጹት ጉቴሬዝ፤ የበለጸጉ አገራት ቀደም ሲል ቃል የገቡትን የፋይናንስ ድጋፍ ተግባራዊ እንዲያደርጉ አስገንዝበዋል። ድርጅቱ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2030 የታዳሽ ሃይል አጠቃቀም በሶስት እጥፍ እንዲያድግ ፍላጎት እንዳለው የተገለጸ ሲሆን ከተፈጥሮ ሃብት ከባቢ ጋር የሚስማሙት የንፋስ፣ የጸሃይ፣ የእንፋሎትና የውሃ ሃይል ምንጮች እንዲስፋፉ እያበረታታ መሆኑንም አሳውቋል። ድርጅቱ የአየር ንብረት መለወጥን ታሳቢ ያደረጉ ስራዎች ለመተግበር የገንዘብ ምንጮች እንዲገኙ አፋጣኝ እርምጃዎች ሊወሰዱ እንደሚገባ ማሳሰቡን የአናዶሉ ዘግቧል።
የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን በአፍሪካ ቀንድ ተጨማሪ የ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዮሮ አስቸኳይ ጊዜ ድጋፍ አደረገ
Nov 30, 2023 109
አዲስ አበባ፤ ህዳር 20/2016(ኢዜአ):- የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን በአፍሪካ ቀንድ ለተከሰተው የጎርፍ አደጋ ተጨማሪ የ3 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዮሮ አስቸኳይ ጊዜ ድጋፍ ማድረጉን አስታውቋል። ኮሚሽኑ ተጨማሪ ድጋፍ የሚያደርገው በሶማሊያ፣ በኢትዮጵያ እና በኬንያ በተከሰቱ የጎርፍ አደጋዎች ለተጎዱ ወገኖች መሆኑን የአውሮፓ ሲቪል ጥበቃ እና የሰብአዊ እርዳታ ስራዎች (ECHO) ትናንት ባውጣው መግለጫ አስታውቋል። ኮሚሽኑ በመግለጫው እንዳመለከተው፤ በሶማሊያ በአሁኑ ወቅት በተከሰተው የጎርፍ አደጋ በተለይም በጁባ ወንዝ ተፋሰስ አካባቢ ለሚገኙ ዜጎች የ2 ሚሊዮን ዮሮ ተጨማሪ ድጋፍ እንደሚደረግም አመልክቷል። ይህም የገንዘብ ድጋፍ በሶማሊያ በቅርቡ በኤልኒኖ ምክንያት በተከሰተው የጎርፍ አደጋ ለተጎዱ እና ለተፈናቀሉ ሰዎች ከዚህ በፊት ከተመደበው 5 ነጥብ 5 ሚሊዮን ዮሮ ሰብአዊ እርዳታ በተጨማሪ የተሰጠ ነው ብሏል መግለጫው። ኮሚሽኑ በኢትዮጵያም በጎርፍ ለተጎዱ አካባቢዎች 1 ሚሊዮን ዮሮ ተጨማሪ ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጾ፤ ድጋፉም ጎርፉ ጉዳት ባደረሰባቸው አካባቢዎች መጠለያ ለመሥራት፣ አስፈላጊ ቁሳቁሶችን ለማከፋፈል፣ የውሃ ማጣሪያ እና ለህክምና አገልግሎት እንደሚውል አስታውቋል። የገንዘብ ድጋፉ በሶማሌ፣ ኦሮሚያ እና ደቡብ ክልሎች በአውሮፓ ህብረት የአደጋ ጊዜ ምላሽ ከጎርፉ በፊት የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን ለመሥራት ከተሰጠው የ2 ነጥብ 3 ሚሊዮን ዮሮ አፋጣኝ እርዳታ በተጨማሪ የተሰጠ መሆኑን ኮሚሽኑ አመልክቷል። ይህም በቅርቡ በኢትዮጵያ ለተከሰተው የጎርፍ አደጋ ምላሽ አጠቃላይ የአውሮፓ ህብረት ያደረገውን የገንዘብ ድጋፍ ወደ 3 ነጥብ 3 ሚሊዮን ዮሮ እንደሚያሳድገው መግለጫው አመልክቷል።
ኢጋድ ና ሱዳን በሀገሪቱ የተፈጠረውን ቀውስ በሚረግብበት ሁኔታ ላይ ለመምክር ተስማሙ
Nov 27, 2023 148
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 17/2016(ኢዜአ)፡- ኢጋድ ና ሱዳን በሀገሪቱ የተፈጠረውን ቀውስ በሚረግብበት ሁኔታ ላይ ለመምክር ተስማሙ። የሱዳን ሉአላዊ የሽግግር መንግስት ሊቀመንበር አብዱልፈታህ አልቡርሃን እና የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት (ኢጋድ) ሊቀመንበር ወርቅነህ ገበየሁ በሱዳን ቀውስ ላይ አስቸኳይ ምክክር ለማድረግ መስማማታቸውን የሱዳን መንግስት አስታወቀ፡፡ አል ቡርሃን በሀገሪቱ የተፈጠረውን ቀውስ ለመፍታት በሚቻልበት ጉዳይ ላይ ከኢጋድ ሊቀመንበር ወርቅነህ ገበየሁ ጋር ለመምከር ፍላጎታቸውን ያሳዩት ከጅቡቲው ፕሬዝዳንት እስማኤል ኦማር ጌሌ በተወያዩበት ወቅት ነው፡፡ አልቡርሃን እና የኢጋድ ሊቀመንበር ምክክራቸውን በሳውዲ አረቢያ እንደሚያደርጉ የተገለፀ ሲሆን የሱዳን ታጣቂ ሃይሎችና ፈጠኖ ደራሽ ሃይሉ በምክክሩ እንደሚገኙም የሱዳን መንግስት መግለጫ አመልክቷል፡፡ በመግለጫው የኢጋድ አስቸኳይ ጉባኤ የሱዳንን አሁናዊ የግጭት ሁኔታ እንዲፈታ ከሁሉም አካላት ስምምነት ላይ ተደርሷል ብሏል፡፡ የአፍሪካ ህብረት የሰላምና የፀጥታ ምክር ቤት ቅዳሜ እለት ባወጣው መግለጫ በሱዳን ያለውን ግጭት አውግዞ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በሀገሪቱ የተኩስ አቁም እንዲደረግ መጠየቁን ሲጂቲኤን ዘግቧል፡፡
ፓኪስታን የብሪክስ/BRICS/ አባል ለመሆን ጥያቄ አቀረበች
Nov 25, 2023 129
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 14/2016 (ኢዜአ) ፦ ፓኪስታን የብሪክስ አባል ሀገራትን ለመቀላቀል ጥያቄ ማቅረቧን የፓኪስታን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ። ብሪክስ ለታዳጊ አገራት ጠቃሚ ቡድን መሆኑንም ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ አመልክቷል። የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ ሙምታዝ ዛህራ ባሎክ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ ፓኪስታን የብሪክስ አባል ለመሆን ጥያቄ ማቅረቧን አረጋግጠዋል። ሀገሪቱ የቡድኑ አባል ለመሆን ጥያቄ ያቀረበችው ቡድኑ ግልጽነት የተሞላበት፣ ብዙሃኑን ያቀፈና አካታች በመሆኑ መሆኑንም ቃል አቀባይዋ ተናግረዋል። በዚህም ፓኪስታን የቡድኑ አባል ብትሆን በቀጣይ ለሚፈጠረው አለም አቀፍ ትብብር ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖራት አብራርተዋል። ፓኪስታን ከብዙዎቹ የብሪክስ አባል ሀገራት እንዲሁም ከአዳዲሶቹ ጥያቄ ያቀረቡ አገራት ጋር ወዳጅነት እንዳላት መግለጻቸውን ዥንዋ አስነብቧል። ቃል አቀባይዋ አክለውም “ቡድኑ ፓኪስታን ያቀረበችው የአባልነት ጥያቄ የትብብርና አብሮ የመለወጥ ፍላጎት የያዘ ጥያቄ መሆኑን መሰረት አድርጎ ቀና ምላሽ እንደሚሰጠን ተስፋ እናደርጋለን" ብለዋል። ብሪክስ በአሁኑ ወቅት በብራዚል፣ ሩሲያ፣ ህንድ፣ ቻይና እና ደቡብ አፍሪካ የተካተቱበት የኢኮኖሚ ቡድን ሲሆን በነሀሴ ወር በደቡብ አፍሪካ በተካሄደው 15ኛው የቡድኑ የመሪዎች ጉባኤ የኢትዮጵያን፣ የኢራንን፣ የአርጀንቲናን፣ የግብፅን፣ የሳዑዲ አረቢያንና የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶችን የአባልነት ጥያቄ መቀበሉ ይታወሳል።
አፍሪካ ከአጋር አከላት ጋር በትብብርና በጋራ ተጠቃሚነት ለመስራት ዝግጁ ናት - ሙሳፋቂ መሃመት
Nov 21, 2023 162
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 11/2016 (ኢዜአ)፦ አፍሪካ በሁሉም ዘርፍ ካሉ አጋር አከላት ጋር በትብብርና በጋራ ተጠቃሚነት ለመስራት ዝግጁ ናት ሲሉ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሳፋቂ መሃመት ተናገሩ። በጀርመን በርሊን በተካሄደው የ'ኮምፓክት ዊዝ አፍሪካ' ጉባኤ ላይ ንግግር ያደረጉት የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሳፋቂ መሃመት አፍሪካ የጋራ ተጠቃሚነት ለሚያረጋግጡ ተግባራት በሯ ክፍት ነው ብለዋል። በአህጉሪቷ ያለውን የኢንቨስትመንት ሀብት በሁለትዮሽ ትብብር በማሳደግ የጋራ ተጠቃሚነትንና ብልጽግናን ለማረጋገጥ ዝግጁ ነን ሲሉም ነው ያረጋገጡት። የአፍሪካ ሀገራት እንደ ጀርመንና ቻይና ካሉ ሀገራት ጋር ሚዛኑን በጠበቀ የሁለትዮሽ ተጠቃሚነት እየሰሩ መሆኑንም አውስተው ''ኮምፓክት ዊዝ አፍሪካ' ጉባኤም በዚህ ረገድ ጉልህ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል። እንደ አህጉር በኢንቨስትመንት መዳረሻዎችና በሌሎች መስኮች የሚታዩ ችግሮችን ለመፍታትም አጋር አካላት በትብብር መስራት እንደሚገባቸው ማመልከታቸውን አፍሪካን ኒውስ ዘግቧል። በ2017 የጀርመን የጂ20 ፕሬዝዳንትነት ዘመን የተጀመረው የጂ20 'ኮምፓክት ዊዝ አፍሪካ' ጉባኤ ለውጥ ተኮር በሆኑ የአፍሪካ ሀገራት፣ በጂ 20 አጋሮች ብሎም ከእነዚህ ባሻገር ባሉ አካላት መካከል የንግግር እና የትብብር መድረክ ሆኗል።
የአፍሪካ የመሬት ፖሊሲ ጉባኤ በአዲስ አበባ ይካሄዳል
Nov 20, 2023 191
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 10/2016 (ኢዜአ) ፦ አምስተኛው የአፍሪካ የመሬት ፖሊሲ ጉባኤ በኢትዮጵያ ተባባሪ አዘጋጅነት ከነገ ጀምሮ ለተከታታይ አራት ቀናት በአዲስ አበባ ይካሄዳል። ጉባኤው “ቀጣይነት ያለው የመሬት አስተዳደር ለአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ፈጣን ትግበራ” በሚል መሪ ሀሳብ በአፍሪካ ሕብረት አዳራሽ እንደሚካሄድም ተጠቁሟል። ጉባኤውን የአፍሪካ የመሬት ፖሊሲ ማዕከል፣ የተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን፣ የአፍሪካ ልማት ባንክ ግሩፕ እንዲሁም የኢትዮጵያ መንግሥት በተባባሪነት እንዳዘጋጁት ተመልክቷል። የአፍሪካ ሀገራትን የመሬት ፖሊሲ ትግበራን በመረጃ፣ ክህሎትና እውቀት ማሳደግ በሚችሉ አጀንዳዎች ላይ መምከር የጉባኤው አላማ እንደሆነም የተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን መረጃ ያመላክታል። ተግባራዊ የተደረጉ የመሬት ፖሊሲ ልምዶችን በመጠቀም ትስስርን መፍጠርና ልምድ መለዋወጥ እንዲሁም የአህጉሪቱን የመሬት ፖሊሲ አቅም ማሳደግም የጉባኤው ሌላኛው አላማ መሆኑ ተመልክቷል።
በዶሚኒካን ሪፐብሊክ በተከሰተ የጎርፍ አደጋ በትንሹ 21 ሰዎች መሞታቸው ተነገረ
Nov 20, 2023 135
አዲስ አበባ ፤ህዳር 10/2016(ኢዜአ)- በዶሚኒካን ሪፐብሊክ እጅግ ከፍተኛ መጠን ያለው ዝናብ ባስከተለው ጎርፍ ህጻናትን ጨምሮ 21 ሰዎች መሞታቸው ተነግሯል። ሁነኛ መፍትሔ ባልተገኘለት የአየር ንብረት ለውጥ የተነሳ በተለያዩ የአለማችን ክፍሎች አስከፊ የተፈጥሮ አደጋዎች እየተከሰቱ ይገኛል። ካሪቢያዊቷ ዶሚኒካን ሪፐብሊክም ባለፉት 48 ሰዓታት ነፋስ ቀላቅሎ በጣለው እጅግ ከፍተኛ ዝናብ መጠነ ሰፊ ጉዳት አስተናግዳለች። ፍራንስ 24 የሀገሪቱን ባለስልጣናትን ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው ዋና ከተማዋ ሳንቶ ዶሚኒጎን እና ሌሎች አካባቢዎችን ባካለለው አደጋ መኖሪያ ቤቶችና መሠረተ ልማቶች ወድመዋል። አደጋው በሰዎች ላይ ባስከተለው ጉዳትም በጉዞ ላይ የነበሩ የአንድ ቤተሰብ አባላትና 3 ህጻናትን ጨምሮ እስካሁን 21 ሰዎች መሞታቸው ተነግሯል። በአንዳንድ አካባቢዎችም የኤሌክትሪክና ሌሎች አገልግሎቶች የተቋረጠ ሲሆን በሚቀጠሉት 24 ሰዓታት የአደጋው ሁኔታ ሊከፋ እንደሚችል ተመልክቷል። በዚህም 13 ሺህ ገደማ ሰዎችን የአደጋ ቀጠና ተብለው ከተለዩ 32 አካባቢዎች ማንቀሳቀሱን የሀገሪቱ የድንገተኛ አገልግሎት ማእከል ገልጿል። ፕሬዚዳንት ልዊስ አቢናዳር ክስተቱን አስመልክተው በሰጡት መግለጫ “የአየር ንብረት ለውጥ እያስከተለ ያለውን ችግር ቸል ያሉ በጉዳቱ ሀገራችን ምስክር ናት፤ በታሪክ እጅግ ከፍተኛ ዝናብ አስተናግደናል” ሲሉ ተናግረዋል። ፕሬዚዳንቱ ትምህርት ቤቶች ለተወሰኑ ቀናት አገልግሎት እንደማይሰጡ ጠቁመው የዜጎችን ደህንነት የሚያረጋግጡ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል።
ጃቪየር ሚሌ የአርጀንቲና ፕሬዝዳንት ሆነው ተመረጡ
Nov 20, 2023 117
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 10/2016 (ኢዜአ) ፦ በአርጀንቲና የተካሄደውን ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ጃቪየር ሚሌ ተቀናቃኛቸውን ሰርጂዮ ማሳን በመብለጥ የአገሪቱን ፕሬዘዳንታዊ ምርጫ አሸነፉ፡፡ ተቀናቃኛቸው የአገሪቱ ኢኮኖሚ ሚኒስትር ሰርጂዮ ማሳ ውጤቱን በጸጋ እንደሚቀበሉና ተመራጩን ፕሬዚደንት እንኳን ደስ ያሉት ለማለት አንደሚያገኟቸው ተናግረዋል፡፡ 90 በመቶ ያህሉ የመራጮች ድምጽ ተቆጥሮ በተገኘ ጊዜያዊ ውጤት ሚሌ ከአምሳ አምስት በመቶ በላይ ድምጽ ሲያገኙ ተቀናቃኛቸው ሰርጂዮ ደግሞ 44 በመቶ ማግኘታቸው ተጠቁሟል፡፡ በዚህም ለቀጣይ አራት አመታት የላቲን አሜሪካዊቷን አገር አርጀንቲናን ለመምራት መመረጣቸውን ነው የቢቢሲ ዘገባ የሚያሳየው። ከውጤቱ በኋላ የምርጫው አሸናፊ ሚሌ በዋና ከተማዋ ቦነስ አይረስ ለተሰበሰቡ ደጋፊዎቻቸው ባደረጉት ንግግር ዛሬ አርጀንቲና እንደገና የምትገነባበት፣ ከውድቀት የምትነሳበት ልዩ ቀን ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በህንድ ዋሻ ውስጥ የሚገኙ 40 ዜጎችን ለመታደግ የነብስ አድን ሰራተኞች ቁፋሮ ሊጀምሩ ነው
Nov 16, 2023 198
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2016(ኢዜአ)፦በህንድ በተደረመሰ ዋሻ ውስጥ የሚገኙ 40 የግንባታ ሰራተኞችን ለመታደግ የነብስ አድን ሰራተኞች ቁፋሮ ሊጀምሩ እንደሆነ የሰሜናዊ ህንድ መንግስት ገልጿል። በሰሜናዊ ህንድ አርባ የግንባታ ሰራተኞች በስራቸው ላይ እያሉ የሚገኙበት ዋሻ አንደኛው ክፍል ተደርምሶ መውጫ ተዘግቶባቸዋል። ሰራተኞቹ በመንገድ ግንባታ ላይ እያሉ የተከሰተው የመሬት መንሸራተት የ 2 ነጥብ 7 ማይል ዋሻ የተወሰነ ክፍል እንዲደረመስ አድርጓል። እስከ አሁን የነብስ አድን ሰራተኞች የምግብና የመድኃኒት አቅርቦት ለሰራተኞቹ እያቀረቡ ሲሆን የአካባቢው ባለስልጣናት ወደ ሰዎቹ ለመድረስ በዋሻው ፍርስራሽ ውስጥ ቁፋሮ ለመጀመር መዘጋጀታቸው ተመላክቷል። በህንድ በሰሜናዊ ግዛት የመሰረተ-ልማትና የልማት ኮርፖሬሽን ባለስልጣን አንሹ ማኒሽ ካሃልኮ የቁፋሮ ስራው ዛሬ እንደሚጀመር ነው ያሰታወቁት። የቁፋሮ ስራዉ በፍጥነት ከተጀመረ ሰራተኞቹን ካሉበት ዋሻ ለማውጣት የሚደረገውን ጥረት እንደሚያፋጥነው ገልጸዋል። የነብስ አድን ሰራተኞቹ ካለፈው አሁድ ጀምሮ በዋሻ ውስጥ የተቀረቀሩ የግንባታ ሰራተኞችን ለማዳን ሰፊ የብረት ቱቦ ወደ ዋሻ ለማስገባት ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ ለዚህም ለቁፋሮ የሚሆንም መሳሪያ በሶስት አውሮፕላኖች ተጭኖ ከኒው ዴሊህ መምጣቱ ተጠቁሟል። ከሰራተኞቹ መካከል አንዳንዶቹ የህመም ስሜት እያጋጠማቸው እንደሆነ ሪፖርት ቢያደርጉም፤ እስከ አሁን የከፋ ጉዳት የደረሰበት ሰራተኛ አለመኖሩ ተገልጿል። በነብስ አድን ኦፕሬሽኑ ከ200 በላይ የነብስ አድን ሰራተኞች እየተሳተፉ ይገኛሉ። የግንባታ ሰራተኞቹ ቤተሰቦችና ጓደኞች ከተደረመሰው ዋሻ አካባቢ ሆነው ሁኔታውን እየተከታተሉ እንደሚገኙና የግዛቲቱ መንግሰት የነብስ አድን ስራውን ማፋጠን በሚቻልበት ሁኔታ ዙሪያ ከህንድ ጦርና ከውጭ የነብስ አድን ባለሙያዎች ጋር እየመከረ ስለመሆኑ ዘ አይሪሽ ኒውስ ዘግቧል።
በሰሜናዊ ቻይና በአንድ ህንፃ ላይ በደረሰ የእሳት አደጋ የ25 ሰዎች ህይወት አለፈ
Nov 16, 2023 126
አዲስ አበባ፤ ህዳር 6/2016(ኢዜአ)፦በሰሜናዊ ቻይና ሻንዚ ግዛት በአንድ የድንጋይ ከሰል አምራች ኩባንያ ህንፃ ላየ በደረሰ የእሳት አደጋ የ25 ሰዎች ህይወት ሲያልፍ በርካቶች በአደጋው ጉዳት ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል፡፡ እንደ ሲጂቲኤን ዘገባ የእሳት አደጋውን በቁጥጥር ስር በማዋል ጉዳት የደረሰባቸውን ሰዎች ወደ አቅራቢያው ሆስፒታል በመውሰድ ተጨማሪ ክትትል እየተደረገላቸው ይገኛል። ንብረትነቱ ዮንጁ የተባለ የድንጋይ ከሰል ማምረቻ ኩባንያ በሆነው ባለ አራት ወለል ህንጻ ላይ ሌሊቱን በተነሳው ቃጠሎ የደረሰው ጉዳት ከፍተኛ መሆኑንና የሟቾቹ ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል ተገልጿል። ከህንፃው 63 ሰዎችን ማስወጣት የተቻለ ሲሆን 51 ሰዎች ወደ ሆስፒታል ተወስደዋል፤ የሟቾቹ ቁጥር ወደ ሆስፒታል ከሄዱት መካከል ስለመሆኑ አለመረጋገጡን ዛገባው አመልክቷል፡፡ እሳቱ ከህንፃው ሁለተኛ ፎቅ እንደተነሳ የዘገበው ደግሞ ዥንዋ የዜና ወኪል ነው፣ እንደዘገባው እሳቱ የፎቁን መላውን ክፍል ማዳረሱን በተለያዩ የማህበራዊ ሚዲያ ገፆች መታየቱን ጠቁሟል።
ዴቪድ ካሜሩን የእንግሊዝ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በመሆን ተሾሙ
Nov 13, 2023 182
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2016(ኢዜአ)፦የቀድሞው የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን የሀገሪቱ አዲስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በመሆን ተሹመዋል። በካቢኔያቸው ሹም ሽር እያደረጉ የሚገኙት የወቅቱ የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ሪሺ ሱናክ ያልተጠበቀ ሹመት መስጠታቸውን ሮይተርስ ዘግቧል። በዚህም እንግሊዝን እ.አ.አ ከ2010 እስከ 2016 በጠቅላይ ሚኒስትርነት የመሩት ዴቪድ ካሜሩንን የሀገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አድርገው መሾማቸውን ነው ዘገባው ያመለከተው። የ57 አመቱ የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ካሜሩን ከ7 ዓመታት በፊት ከፖለቲካው መድረክ በመራቅ በቢዝነስ ስራ ላይ ተሰማርተው መቆየታቸው ተዘግቧል።
የአፍሪካ አቬሽን ባለሙያዎች የዘርፉን ትርፋማነት በሚያሳድጉ ሁኔታዎች ዙርያ ሊመክሩ ነው
Nov 13, 2023 165
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2016(ኢዜአ)፦የአፍሪካ አቬሽን ባለሙያዎች የዘርፉን ትርፋማነት ለማሳደግ በሚያስችሉ ጉዳዮች ዙርያ እንደሚመክሩ ተገለጸ። 55ኛው የአፍሪካ አየር መንገዶች ሕብረት አመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ በሚቀጥለው ሳምንት በዩጋንዳ ካምፓላ ይካሄዳል። ከ500 በላይ የዘርፉ ተዋንያን እንደሚሳተፉበት በሚጠበቀው ይህ ጠቅላላ ጉባኤ በአቬሽን ዘርፉ ከፍተኛ የቢዝነስ ትስስርን ለመፍጠር ያለመ ነው ። የዩጋንዳ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ ጄኔፈር ባሙቱካሪ እንደተናገሩት በጉባኤው ከ30 በላይ አየር መንገዶች የሚሳተፉ ሲሆን አፍሪካ ያላትን እምቅ አቅም ለማሳደግ የሚችሉ ሀሳቦች እንደሚነሱበት ይጠበቃል። በጉባኤው የአቬሽን ዘርፍ ከፍተኛ ባለሙያዎች የሚሳተፉበት ምክክርም እንደሚካሄድ ተናግረው የአፍሪካ አየር መንገዶች በዘርፉ ትርፋማነትን ማሳደግ የሚችሉበት ውይይት የጉባኤው ዋና አጀንዳ መሆኑን ገልጸዋል። በአህጉሩ ከአንድ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር የሚደረግ በረራን በነጻ ቀጣና ማካሄድም የጉባኤው ሌላው የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን አብራርተዋል። ሴቶች በአቬሽን ዘርፉ ያላቸውን ተሳትፎ ማሳደግም ና የሴቶች አቬሽን ማህበር ማቋቋምም ተጨማሪ የጉባኤው አጀንዳ መሆኑን ጠቁመዋል። የአፍሪካ አየር መንገዶች ሕብረት አመታዊ ጉባኤ በዘርፉ ከሚካሄዱ ግዙፍ ጉባኤዎች ግንባር ቀደሙ መሆኑን ደይሊ ሞኒተር ዘግቧል።
የአፍሪኤግዚም ባንክ ለአፍሪካ የፊልም ኢንዱስትሪዎች 1 ቢሊዮን ዶላር ድጋፍ ሊያደርግ ነው
Nov 13, 2023 159
አዲስ አበባ፤ ህዳር 3/2016(ኢዜአ)፦የአፍሪካ ኢምፖርት ኤክስፖርት ባንክ (አፍሪኤግዚም) የአፍሪካ የፊልም ኢንዱስትሪዎችን ለመደገፍ አንድ ቢሊዮን ዶላር መመደቡን ገለጸ። የባንኩ ምክትል ዋና ስራ አስፈጻሚ ካናዮ አዋኒ በግብጽ በተካሄደ የአፍሪካ የንግድ ጉባኤ እንደተናገሩት የአፍሪካ ኢምፖርት ኤክስፖርት ባንክ በአህጉሪቱን የፊልም ኢንዱስትሪዎችን አቅም ለማሳደግ የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። እ.አ.አ በ2022 ባንኩ ለአፍሪካ የሙዚቃ፣ ፊልም፣ ስፖርትና ሌሎች ኪነጥበባዊ ዘርፎች 600 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን ገልጸዋል። ከወራት በኋላ በሚጀምረው የፈረንጆቹ አዲስ አመትም ለአፍሪካ የፊልም ኢንዱስትሪዎች በስቱዲዮ ግንባታ፣ ፊልም ቀረጻ እንዲሁም ለፊልም ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያ የሚውል አንድ ቢሊዮን ዶላር ድጋፍ ለማድረግ መዘጋጀቱን አስታውቀዋል። ለአብነትም በ2024 አየር ላይ ለሚውሉ የደቡብ አፍሪካ፣ ኬኒያና ናይጄሪያ ፊልሞች የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን ገልጸዋል። በሴክተሩ የሚታየውን የመሰረተ ልማትና ቴክኖሎጂ፣ የገበያ ተደራሽነት እንዲሁም የብቁ ባለሙያ ችግርን ለመቅረፍ የአፍሪካ ኢምፖርት ኤክስፖርት ባንክ እየሰራ እንደሚገኝ ምክትል ዋና ስራ አስፈጻሚው መናገራቸውን ናይጄሪያን ትሪቡን ዘግቧል። የአፍሪካ የፊልም ኢንዱሰትሪ በየአመቱ ከጠቀላላ የሀገር ውስጥ ምርት 5 ቢሊዮን ዶላር ገቢ የሚያስገኝ ሲሆን ከ5 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎችም የስራ እድል መፍጠሩን በመረጃው ተመልክቷል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በሳዑዲ-አፍሪካ ጉባዔ ላይ ያደረጉት ንግግር ፋይዳው የጎላ መሆኑን የሳዑዲ ጋዜጣ ገለጸ
Nov 11, 2023 147
አዲስ አበባ ፣ህዳር 1/2016(ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በሳዑዲ-አፍሪካ ጉባዔ ላይ ያደረጉት ንግግር ፋይዳው የጎላ መሆኑን የሳዑዲ ጋዜጣ ዘግቧል። በሳዑዲ - አፍሪካ ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ንግግር አድርገዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ የአፍሪካንና ሳዑዲ አረቢያ ታሪካዊ ግንኙነት ማንሳታቸውንና የሳዑዲ-አፍሪካ ግንኙነት ለማጠናከር በርካታ አቅሞች እንዳሉም መግለጻቸውን ጠቅሷል። ሳዑዲ አረቢያ በአፍሪካ ወሳኝ ዘርፎች ላይ መዋዕለ ንዋይ ለማፍሰስ ያላት ቁርጠኝነት የሚደነቅ ነው ሲሉ መግለጻቸውንም በዘገባው አስፍሯል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በንግግራቸው ሳዑዲ አረቢያ በአፍሪካ በታዳሽ ኢነርጂ፣ በመሰረተ ልማት፣ በግብርና፣ በጤናና በትምህርት ዘርፍ መዋለ ንዋይን ለማፈሰስ እያሳያች የለው ቁርጠኝነት የሚደነቅ ነው፡፡ ኢትዮጵያና ሳዑዲ አረቢያ የረጅም ዓመታት መልካም ግንኙነት ያላቸው አገሮች መሆናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትሩ መግለጻቸውንም ጠቅሷል። ኢትዮጵያ ከሳዑዲ አረቢያ ጋር ያላትን ኢኮኖሚያዊ ትብብር ይበልጥ ማሳደግ እንደምትፈልግም ማንሳታቸን በዘገባው አስፍሯል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የግብርናው ሴክተር የኢትየጵያ ዋና የአኮኖሚ መሰረት መሆኑን ጠቅሰው የሳዑዲ ኢንቨስተሮች በግብርናው ዘርፍ መዋለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ የሁለቱን አገራት የጋራ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጥ የተለያዩ ዘርፎች ላይ በጋራ ለመስራት ኢትየጵያ ቁርጠኛ መሆኗን መግለጻቸውንም በዘገባው ተመልክቷል፡፡