ዓለም አቀፍ ዜናዎች
ፕሬዝዳንት ፑቲን ለአፍሪካ ህብረት 60ኛ ዓመት የምስረታ በዓል የእንኩዋን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላለፉ
May 25, 2023 220
አዲስ አበባ ግንቦት 17/2015 (ኢዜአ)፦የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሜር ፑቲን ለቀድሞው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ለአሁኑ የአፍሪካ ህብረት 60ኛ ዓመት የምስረታ በዓል የእንከዋን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። ፕሬዝዳንቱ ባስተላለፉት የእንኩዋን አደረሳችሁ መልዕክት የቀድሞው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ የአፍሪካ ህብረት ለአፍሪካውያን የድል ምልክት ነው ያሉ ሲሆን የአፍሪካውያን የነጻነት፣የሰላምና የብልጽግና ፍላጎት ማሳያ ነው ብለዋል። ህብረቱ ከተመሰረተበት ግዜ አንስቶ ለብዙ አስርተ ዓመታት በዓለም አቀፍ መድረኮች አፍሪካውያንን በመወከል የባለብዙ ወገን ውይይቶችንና ትብብርን በማጎልበት ትልቅ ሚና ተጫውቷል ብለዋል። የአፍሪካ ሀገራት ለችግሮቻቸው በጋራ ምላሽ የሚሰጡበትን መንግድ ያመቻቸ መሆኑን ጠቁመው አህጉራዊ ትብብርን በተለያዩ መስኮች እንዲያጠናከሩም መንገድ ከፍቷል ብለዋል። በዚህም ለአፍሪካ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት የላቀ ሚና ማበርከቱንና አፍሪካ በዓለም አቀፍ ጉዳዮች ያላትን ተሳትፎ እንድታሳድግ ህብረቱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ገልጸዋል። በመሆኑም ሩሲያ ከአፍሪካ አጋሮቿ ጋር ያላትን ወዳጅነት ለማጠናከር ልዩ ትኩረት ትሰጣለች ያሉት ፕሬዝዳንቱ እ.አ.አ በ2019 የተካሄደው የመጀመሪያው የአፍሪካ -ሩሲያ ጉባኤ በአፍሪካና በሩሲያ መካከል ያሉ ትብብሮች እንዲጠናከሩ አስችሏል ብለዋል። በመጪው ሃምሌ ወር በሩሲያ የሚካሄደው ሁለተኛ የአፍሪካ ሩሲያ ጉባኤም ሩሲያ ከአፍሪካ ጋር ለሚኖራት ትብብር አዲስ ምዕራፍ እንደሚፈጥር ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።
ተመድ በሶሪያ በርዕደ መሬት ለተፈናቀሉ ዜጎች የሚውል የ397 ሚሊየን ዶላር ድጋፍ ጥሪ አቀረበ
Feb 15, 2023 3780
አዲስ አበባ (ኢዜአ) የካቲት 8/2015 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሓፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ በሶሪያና ቱርክ ድንበር አቅራቢያ በደረሰው ርዕደ መሬት ሳቢያ ከቤታቸው የተፈናቀሉ ሶሪያውያንን ለማገዝ የ397 ሚሊየን ዶላር ድጋፍ ጥሪ አቀረቡ። ዋና ጸሓፊው ጥሪውን ያቀረቡት ባሳለፍነው ሳምንት በቱርክና በሶሪያ ድንበር አቅራቢያ በደረሰው ርዕደ መሬት ሳቢያ ከቤታቸው የተፈናቀሉ አምስት ሚሊዮን የሚጠጉ ሶሪያውያንን ለማገዝ ነው። በኒውዮርክ በሰጡት መግለጫ ሶሪያውያኑን ለማገዝ የተጠቀሰው የገንዘብ መጠን ለሶስት ወራት ጊዜ ብቻ የሚበቃ መሆኑን ጠቅሰው የሚመለከታቸው ሁሉ የድርሻቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል። ከአደጋው በኋላ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት 50 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር አስቸኳይ ድጋፍ ማቅረቡን ገልጸው ተጨማሪ እገዛዎች አሁንም እንደሚያስፈልጉ አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል። በድርጅቱ ስር የሚገኙ የተለያዩ ተቋማትና አጋር አካላት በጋራ በሚያቀርቡት ገንዘብ፤ አስቸኳይ ድጋፍ ለሚፈልጉ ሶሪያውያን የመጠለያ፣ የጤና፣ የምግብ እንዲሁም ሌሎች አስቸኳይ ድጋፎች እንደሚደረጉ አብራርተዋል። ተመሳሳይ የድጋፍ ማዕቀፍ በቱርክ ድንበር ለሚገኙ ዜጎች እየተጠናቀቀ እንደሚገኝም ዋና ጸሓፊው ተናግረዋል።
የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ከባህረ-ሰላጤው ሀገራት ጋር ያለውን ኢኮኖሚያዊ ትስስር እያሳደገው እንደሚገኝ ተገለጸ
Dec 20, 2022 1653
አዲስ አበባ ታኅሳስ 11/2015 (ኢዜአ) አህጉራዊው የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና አፍሪካ ከባህረ-ሰላጤው ሀገራት ጋር ያላትን የንግድ ግንኙነትና ኢኮኖሚያዊ ትስስር እያሳደገው እንደሚገኝ ተመላከተ። የተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ ከአፍሪካ ጋር ያላት የንግድ ትስስር ከባህረ-ሰላጤው ሃገራት መካከል በቀዳሚነት እንደሚጠቀስም ተገልጿል። የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ዋና ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ዊሊያም ስቴንሀውስ ከሲ ጂ ቲ ኤን ጋር በነበራቸው ቆይታ የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ በተለይም ዱባይ የአፍሪካን ንግድና ኢንቨስትመንት በተመለከተ ዋና ማዕከል ሆናለች ብለዋል። በዱባይ 25ሺህ ገደማ የአፍሪካ ካምፓኒዎች እንደሚንቀሳቀሱ አመልክተው ይህም ሀገሪቱ በነጻ የንግድ ቀጣናው የቢዝነስ አጋር እንድትሆን አስችሏታል ነው ያሉት። አፍሪካውያን ባለሃብቶች የግብይት ማዕከላቸውን በተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ በማድረግና ምርቶችን ወደ አህጉሪቷ በማስገባት በነጻ ንግድ ቀጣናው ስር የገልፍ ሀገራትን ኢኮኖሚያዊ ትስስር እያሳደጉት እንደሚገኝም አስገንዝበዋል። የዱባይ ወደብ በአፍሪካ ያለው ተደራሽነት መስፋፋትም አፍሪካ ከባህረ ሰላጤው ሀገራት ጋር የሚኖራትን የሎጀስቲክስ አቅርቦት እንደሚያሳድግ በመረጃው ተመላክቷል። ከገልፍ ሀገራት ጋር ያለው ግንኙነት ከኢኮኖሚያዊ ትስስር ባለፈ ዲፕሎማሲያዊና ወንድማማችነትን መሠረት ያደረገ ነው ያሉት ደግሞ በተባበሩት አረብ ኤሜሬት የኢትዮጵያ ባለ ሙሉ ስልጣን አምባሳደር ሱሌማን ደደፎ ናቸው። አምባሳደሩ እንደሚሉት ከመካከለኛው ምስራቅ መነሻቸውን ያደረጉ ባለሃብቶችና የቢዝነስ ሰዎች ከምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ጋር በልዩ ልዩ ዘርፎች ግንኙነታቸውን እያጠናከሩ ይገኛል። እ.አ.አ በጥር 2021 ተግባራዊ መሆን የጀመረው የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና ከአጀንዳ 2063 ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ ነው። የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና የአህጉሪቱን ወሳኝ የኢኮኖሚ ዘርፎች ማለትም የዲጂታል ንግድ፣ የኢንቨስትመንት ትስስርና ሌሎች የንግድ ግንኙነቶችን በነጻ የንግድ ቀጣና ለማከናውን የተካሄደ ስምምነት ነው።
ኢትዮጵያ እና ፓኪስታን የአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖን ለመከላከል በጋራ እንደሚሰሩ ገለጹ
Nov 25, 2022 438
ህዳር 16 / 2015 (ኢዜአ) ኢትዮጵያና ፓኪስታን የአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖ የሚያስከትለውን ችግር ለመከላከል በጋራ እንደሚሰሩ አስታወቁ፡፡ በፓኪስታን የኢትየጵያ አምባሳደር ጀማል በከር ከፓኪስታን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ቢልዋል ቡቶ ዛርዳሪ ጋር በሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ዙሪያ ተወያይተዋል። በውይይታቸውም ሁለቱ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖን ለመከላከል በሚያስችላቸው ሁኔታ ላይ በጋራ ለመስራት ተስማምተዋል፡፡ የሀገራቱን ሁለትዮሽ ግንኙነት በማጠናከር ቀጣናዊና ዘርፈ ብዙ ሆኖ እንዲቀጥል እንደሚሰሩም ገልጸዋል፡፡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ አነሳሽነት እየተሰራ ያለውን የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር ልምድ ለፓኪስታን ለማጋራት እንደሚሰራም አምባሳደሩ አስታውቀዋል፡፡ የፓኪስታን ባለሃብቶች ሊሰማሩባቸው የሚችሉባቸውን የንግድ ዘርፎች ያብራሩት አምባሳደር ጀማል ፓኪስታን ቡና፣ ሻይ፣ የቅባት እህሎችና ጥራጥሬ ከኢትዮጵያ ማስገባት እንደምትችል ገልጸውላቸዋል። በአንጻሩ ፓኪስታን የህክምና፣ የኮንስትራክሽን፣ የጨርቃ-ጨርቅ፣ የስኳርና የመድሃኒት ውጤቶችን ወደ ኢትዮጵያ መላክ እንደምትችል በመጠቆም፡፡ አምባሳደር ጀማል የኢትዮጵያ መንግስት ከአየር ንብረት ለውጥ ተፅእኖ ጋር ተያያዥነት ያላቸው የጎርፍ አደጋ፣ የምግብ ደህንነት ችግሮችን በተመለከተም ከፓኪስታን መንግስት ጋር በጋራ እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡ ፓኪስታን በተለያዩ ጊዜያት በኢትዮጵያ ላይ የሚደረጉ ተፅእኖዎችን በመቃወም ላሳየችው አጋርነትም አምባሳደሩ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ የፓኪስታን የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ቢልዋል ቡቶ ዛርዳሪ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት ችግር በገጠማት ወቅት ኢትዮጵያ ላሳየችው አጋርነት አመስግነዋል። እንዲሁም ኢትዮጵያ በፓኪስታን ኤምባሲዋን መክፈቷ የሁለቱን ሀገራት የሁለትዮሽ፣ ቀጣናዊና ባለብዙ ወገን ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ መልካም ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አክለውም በኢትዮጵያ እና ፓኪስታን መካከል የሚደረገው ቀጥታ በረራ በፓኪስታንና በአፍሪካ መካከል ያለውን ትብብር በማሳደጉ በኩል አዲስ የትብብር ምዕራፍ ይፈጥራል ሲሉም ገልጸዋል።
በአየር ንብረት ለውጥ ሰለባ ለሚሆኑ ታዳጊ አገራት ማካካሻ የሚያደርግ ልዩ ፈንድ ፀደቀ
Nov 20, 2022 372
አዲስ አበባ (ኢዜአ) ህዳር 11 ቀን 2015 የበለጸጉ ሀገራት በሚለቁት ካርበን ምክንያት በሚደርሰው ብክለት ለሚጎዱ ታዳጊ አገራት ማካካሻ የሚያደርግ ልዩ ፈንድ እንዲቋቋም የተባበሩት መንግሥታት የአየር ንብረት ጉባዔ ወሰነ። በግብፅ ሻርም ኤል-ሼክ ሲካሄድ የሰነበተው የአየር ንብረት ጉባዔ (COP-27) 'ኪሳራ እና ጉዳት' የተሰኘ ልዩ የማካካሻ ፈንድ እንዲቋቋም በማጽደቅ ዛሬ ተጠናቋል። ልዩ ፈንዱ በበለጸጉ አገራት በጋዝ ልቀት ሳቢያ በሚከሰተው የሙቀት መጨመር በታዳጊ አገራት ላይ የሚያስከትለውን ጉዳትና ኪሳራ የሚሸፍን ነው ተብሏል። በተሳታፊ አገራት ሌሊቱን ሰፊ ክርክር የተካሄደበት ይኸው ፈንድ በመጨረሻም ታዳጊ አገራት ባቀረቡት ጠንካራ የመከራከሪያ ሃሳብ አጠቃላይ ስምምነት ላይ ተደርሶ ሊጸድቅ ችሏል። በዚህም የበለጸጉ አገራት በአየር ንብረት ላይ የሚያሳድሩትን ተጽዕኖና ወጭዎችን ለመሸፈን የሚያስችል የ"ኪሳራ እና ጉዳት" ልዩ ፈንድ መጽደቁን የቲአርቲ ወርልድ ዘገባ አመላክቷል።" የኪሳራ እና ጉዳት” ልዩ ፈንድ እንዲቋቋም መወሰኑ በአየር ንብረት ቀውስ ምክንያት ህይወታቸው፣ ኑሯቸው እና ባህላቸው ለጉዳት የተዳረገባቸው ማኅበረሰቦችን ለመደገፍ ትልቅ እርምጃ ነው ሲሉ የመንግሥታቱ ድርጅት ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ አወድሰዋል።
የቡድን 20 አባል ሀገራት የመሪዎች ጉባኤ ነገ ይጀመራል
Nov 14, 2022 544
አዲስ አበባ (ኢዜአ) ህዳር 5/2015 17ኛው የቡድን 20 አባል ሀገራት የመሪዎች ጉባኤ ነገ በኢንዶኔዢያ ባሊ ይጀመራል። ጉባኤው “በጋራ እናገግም በጋራ እንጠንከር” በሚል መሪ ሀሳብ ይካሄዳል።ኢንዶኔዢያ በፕሬዝዳንትነት በምትመራው ስብሰባ የዓለም የጤና ስርዓት፣ዘላቂ የኢነርጂ ሽግግር እና የዲጂታል ለውጥ ዋና የውይይት አጀንዳዎች መሆናቸውን የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን በመዘገብ ላይ ናቸው። የኮቪድ-19 ወረርሽኝ፣አነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን ያሳተፈ ሁሉን አቀፍ የኢኮኖሚ ልማትና ዲጂታል ኢኮኖሚ ሌሎች ምክክር ይደረግባቸዋል ከተባሉ ጉዳዮች መካከል መሆናቸው ተጠቅሷል። ጉባኤው ለሁለት ቀናት የሚቆይ ሲሆን የሀገራቱ መሪዎች በስብሰባው ላይ ለመሳተፍ ወደ ኢንዶኔዢያ በመግባት ላይ ናቸው። ቡድን 20 እ.አ.አ 1991 በጀርመን ኮሎኝ ከተማ በእስያ አህጉር የተከሰተውን የፋይናንስ ቀውስ ተከትሎ 20 የዓለም የበለጸጉና በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት የፋይናንስ ሚኒስትሮችና ማዕከላዊ ባንኮችን ለማስተሳሰር ተቋቋመ። ከምስረታው 10 ዓመት በኋላ ውይይቱ ወደ ሀገራት መሪዎችና መንግስት እንዲያድግ ተደርጓል። ቡድን 20 አስራዘጠኝ ሀገራት እና የአውሮፓ ሕብረትን በአባልነት ያቀፈ ነው። አሜሪካ፣ቻይና፣ሩሲያ፣ቱርክ፣ዩናይትድ ኪንግደም፣ሳዑዲ አረቢያ ፣ ካናዳ ፣ ብራዚል ፣ሕንድ፣ደቡብ ኮሪያ፣ጀርመን፣ፈረንሳይ፣ አውስትራሊያ ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ጣልያን ፣ ጃፓን ፣ ሜክሲኮ አርጀንቲናና ኢንዶኔዢያ አባል ሀገራቱ ናቸው።
ቻይና ያደጉ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመከላከል ቃል የገቡትን 100 ቢሊዮን ዶላር እንዲያሟሉ ጥሪ አቀረበች
Nov 9, 2022 385
ጥቅምት 30/2015(ኢዜአ) ቻይና ያደጉ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመከላከል ቃል የገቡትን 100 ቢሊዮን ዶላር ድጋፍ እንዲያሟሉ ጥሪ አቀረበች። በግብጽ ሻርም አል ሼክ እየተካሄደ በሚገኘው የተመድ የአየር ንብረት ጉባኤ ላይ ንግግር ያደረጉት የቻይና የአየር ንብረት ለውጥ ልዩ ተወካይ ዢ ዚንኋ የበለጸጉ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ቃል የገቡትን ድጋፍ እንዲያሟሉ ጠይቀዋል። አለም በአሁኑ ወቅት በአየር ንብረት ለውጥ የተነሳ ዘርፈ ብዙ ቀውሶችን እየተጋፈጠች ትገኛለች ያሉት ዢ በተለይም በኃይልና በምግብ አቅረቦት ረገድ ያጋጠሙንን ችግሮች በመተባበርና በአንድነት ከመፍታት ውጪ አማራጭ የለንም ሲሉ አመልክተዋል። ችግሩን ለመቅረፍ ሁላችንም የተለያየ ኃላፊነት አለብን ሲሉም ገልጸው የበለጸጉ ሀገራት የፓሪሱን ስምምነት ሙሉ በሙሉ እንዲተገብሩ አሳስበዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተጽዕኖ መከላከያ ፕሮጀክቶችን በመተግበር ረገድ ቁልፍ ሚና የሚጫወተውንና ቃል የገቡትን 100 ቢሊዮን ዶላር በአስቸኳይ እንዲያሟሉም ጠይቀዋል። ቻይና የካርቦን ልቀትን ለመቀነስ የወጣውን አለማቀፋዊ ድንጋጌ ለመተግበር እየሰራች እንደምትገኝም አንስተው ሁሉም ሀገራት የአየር ንበረት ለውጥ ተጽዕኖን ለመከላከል አለም አቀፍ ድንጋጌዎችን በመጠበቅ በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል ብለዋል።
የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ተማሪው ደቡብ ሱዳናዊ በሃገራቸው በመስኖና ውሃ ሃብት ሚኒስትርነት ተሾሙ
Nov 8, 2022 362
ጥቅምት 29/2015(ኢዜአ) በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛ ዲግሪያቸውን በመከታተል ላይ ያሉት ደቡብ ሱዳናዊ በሃገራቸው የመስኖ እና የውኃ ኃብት ሚኒስትር ሆነው ተሾሙ። የደቡብ ሱዳን ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ትናንት ማምሻውን ይፋ ባደረገው ዘገባ ፓል ማዊ ዴንግ የመስኖ እና የውኃ ኃብት ሚኒስትር ሆነው እንዲያገለግሉ በፕሬዝዳንት ሳልቫ ኪር ሚያርዲት ተሹመዋል። ቀደም ሲል የደቡብ ሱዳን የመስኖ እና የውኃ ኃብት ሚኒስትር ሆነው ሲያገልገሉ የነበሩት ማናዋ ፒተር ጋትኩኦት ባለፈው ሰኔ ግብጽ መዲና ካይሮ ውስጥ ከልብ ህመም ጋር በተያያዘ ያልተጠበቀ ህልፈታቸው መሰማቱ የሚታወስ ነው። ፓል ማይ ዴንግ በኢትዮጵያ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛ ዲግሪ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ መሆናቸውን ከዩኒቨርሲቲው የተገኘ መረጃ ያስረዳል። አዲሱ የፓል ማይ ዴንግ ሹመት ማናዋ ፒተር ጋትኩኦት ህልፈት ከተሰማ ከአምስት ወር በኋላ የተሰጠ መሆኑን የደቡብ ሱዳን ምንጮች ይፋ አድርገዋል። ፖል ማዊ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውንም አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በፐብሊክ አድሚኒስትሬሽን ማጠናቀቃቸው ታውቋል።
የአሜሪካ አጋማሽ ዘመን ምርጫ ዛሬ ይካሄዳል
Nov 8, 2022 386
ጥቅምት 29/ 2015 (ኢዜአ) 23ኛው የአሜሪካ አጋማሽ ዘመን ምርጫ(ሚድ ተርም ኢሌክሽን) ዛሬ ይካሄዳል። ለአሜሪካ ህግ አውጪ ምክር ቤት (ኮንግረስ) 435 መቀመጫዎችና ከአስፈጻሚው (ከሴኔቱ) 100 መቀመጫዎች ውስጥ 34ቱ (አንድ ሶስተኛው) ለምርጫ ይቀርባሉ። በምርጫው የኢትዮጵያና አሜሪካ የሁለትዮሽ ግንኙነት በማጠናከር የኢትዮጵያን ጥቅም ያስጠብቃሉ ያላቸውን 28 የሴኔትና ኮንግረስ እጩዎች(ሪፐብሊካንና ዴሞክራት ፓርቲ) ይሁንታ (ኢዶርሰመንት) መስጠቱን ኢዜአ ከ’አሜሪካን ኢትዮጵያን ፐብሊክ አፌርስ ኮሚቴ’(ኤፓክ) የተሰኘው የፖለቲካ ተግባር ኮሚቴ ያገኘው መረጃ ያሳያል። በተጨማሪም ለግዛት አስተዳዳሪነትና ለከንቲባነት እንዲሁም ማዘጋጃ ቤታዊ (City council) እና አውራጃ (County) ምርጫ ለሚወዳደሩ 13 እጩዎች ድጋፍ ማድረጉን ገልጿል። እጩዎቹ እውቅና የተሰጣቸው የፖለቲካ ፓርቲን መሰረት በማድረግ ሳይሆን የኢትዮጵያና አሜሪካ የሁለትዮሽ ግንኙነት ያጠናክራሉ በሚል እምነት እንደሆነ አመልክቷል። በተጨማሪም ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በብዛት የሚኖሩባቸው አካባቢዎችን ታሳቢ በማድረግ በ21 ግዛቶች ብሔራዊ የምርጫ ኮሚቴዎች ተቋቁመው ሲሰሩ ቆይተዋል። እጩዎችን የመምረጥና የመወሰን መብት የመራጮች ቢሆንም ተወዳዳሪዎቹ የማሸነፍ እድላቸው የተሻለ የሚባል እንደሆነ ነው ኤፓክ ያስታወቀው። ድጋፍ የተሰጣቸው እጩዎች ቢመረጡ በአሜሪካ ሕግ አውጪ ምክር ቤቶች የኢትዮጵያ ደጋፊ ስብስብን (ኮከስ) ለማጠናከር ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገልጿል። ኤፓክ መምረጥ የሚችሉ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በምርጫው ቀን ድምጻቸውን እንዲሰጡ ጥሪ አቅርቧል። የአሜሪካ አጋማሽ ዘመን ምርጫ(ሚድ ተርም ኢሌክሽን) በየሁለት ዓመቱ የሚካሄድ ነው። በኮንግረስ ምርጫ የሚያሸንፍ እጩ ለሁለት ዓመት እንዲሁም የሴኔት ተወዳዳሪ ለስድስት ዓመት ይቆያል።
የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖን ለመከላከል ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ወዳጅነት ስምምነት አሳቤ ተፈጻሚ እንዲሆን ማድረግ አለባቸው-አንቶኒዮ ጉተሬዝ
Nov 7, 2022 361
አዲስ አበባ ኢዜአ ጥቅምት 28/2015 የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖዎችን ለመከላከልና ለመቀነስ ሀገራት የአየር ንብረት ለውጥ ወዳጅነት ስምምነት እሳቤን ተፈጻሚ ማድረግ አለባቸው ሲሉ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ ተናገሩ። በግብጽ ሻርም አል ሼክ በመካሄድ ላይ የሚገኘውን 27ኛውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የአየር ንበረት ለውጥ ጉባኤ (ኮፕ-27) መክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት ዋና ጸሐፊው "በሚቀጥሉት10 ዓመታት አለማችን ከፍተኛ በሆነ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖዎች ውስጥ ታልፋለች" ብለዋል። "የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖንን በትብብር መግታት ካልተቻለ የሰው ልጆች ሲኦላማ ወደ ሆነ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖ ጎዳና ማምራታቸው አይቀሬ ነው" ሲሉ አሳስበዋል። አለማችን በሚቀጥሉት አስር ዓመታት ውስጥ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖዎችን ማሸነፍ ወይ መሸነፍ አማራጮች ውስጥ ታልፋለች ብለዋል። ሀገራት ሁለት አማራጮች አሏቸው ያሉት ዋና ጸሐፊው ታሪካዊ የሆነውን የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖ የወዳጅነት ስምምነት እሳቤን ተግባራዊ በማድረግ የበካይ ጋዝ ልቀትን በመቀነስ የካርበን ልቀትን ዝቅ ለማድረግ ወይም አለማችንን ከፍተኛ ለሆነ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖዎች ለመዳረግ አማራጭ አላቸው ሲሉ ተናግረዋል። አለም የበካይ ጋዝ ልቀትን ለመቀነስ፣ንጹህ ሃይልን በማመንጨት ዝቅተኛ የካርበን ልቀት ቴክኖሎጂን ለማረጋገጥ እድሎች አሏት ያሉት ዋና ጸሐፊው የአየር ንብረት ለውጥ ትግሉ በሚቀጥሉት 10 ዓመታት ውስጥ ውደ አሸናፊነት እንዲያድግ ሀገራት ለወዳጅነት ስምምነቱ እሳቤ መተግበር መስራት አለባቸው ብለዋል። በግብጽ በመካሄድ ላይ በሚገኘው 27ኛው የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድን ጨምሮ የተለያዩ ሀገራት መሪዎች እየተሳተፉ ይገኛል። ትናንት በሻርም አል ሼክ ከተማ የተጀመረው 27ኛው የአየር ንብረት ጉባኤ እስከ ሕዳር 9 ቀን 2015 ዓ.ም የሚቆይ ሲሆን ከ190 አገራት ይሳተፉበታል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ2022 የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ መሆኑ ተገለጸ
Oct 14, 2022 493
ጥቅምት 4/2015/ኢዜአ/ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የ2022 ከአፍሪካ ምርጥ 10 አየር መንገዶች መካከል አንደኛ ደረጃን በመያዝ ግንባር ቀደምነቱን ማስቀጠሉ ተገለጸ። እንደ ቢዝነስ ኢንሳይደር አፍሪካ ዘገባ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ምቹ፣ ተመራጭና አስተማማኝ የበረራ አገልግሎት በመስጠት ለተከታታይ ሁለት ዓመታት የ1ኛ ደረጃን በመያዝ የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ መሆኑን አረጋግጧል። ከ1ኛ እስከ 10ኛ ያለውን ደረጃ ከያዙት የአፍሪካ አየር መንገዶች መካከል ሁለቱ የብሔራዊ አየር መንገድ እንዳልሆኑ በዘገባው ተመላክቷል። የአየር ትራንስፖርት ምቹ፣ የተቀናጀ፣ ተመራጭና ፈጣን መጓጓዣ መሆኑ ዓለም አቀፋዊ መስተጋብር የተሳለጠ እንዲሆን ትልቅ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። አየር መንገዶች የጉዞ አግልግሎታቸውን ምቹ፣ ደህንነቱ የተጠበቀና ደንበኞቻቸውን ዘና የሚያደርጉ ሥርዓቶችን በመፍጠር የንግድ ውድድርን ለማድረግ ሲተጉ ይስተዋላል። በዚህም "ስካይትራክስ ወርልድ ኤርላይን አዋርድ" አየር መንገዶች የሰጡትን የአገልግሎት ጥራት በመገምገም በዓለም አቀፍ ደረጃ የእውቅና ሽልማት የተሰጣቸውን የምርጥ አየር መንገድ ዝርዝር ይፋ ያደርጋል። የምርጥ አየር መንገድ ዝርዝሩ በዓለም አቀፍ ደረጃ ትልቅ የተባለውን ዓመታዊ የአየር መንገድ ተሳፋሪ የእርካታ የዳሰሳ ጥናት ውጤት መሰረት ያደረገ ነው። እ.አ.አ. ከመስከረም 2021 እስከ ነሐሴ 2022 ድረስ በርካታ የዳሰሳ ጥናት ግብዓቶችን በመጠቀም የመጨረሻ ውጤት ይፋ ተድርጓል። በጥናቱ መሰረት ለሀገራቸው አመርቂ ውጤት ያስመዘገቡ 10 ምርጥ የአፍሪካ አየር መንገዶች ይፋ ሆነዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓለም አቀፍ ደረጃ ምቹ፣ ተመራጭና አስተማማኝ የበረራ አገልግሎት በመስጠት ቁጥር አንድ የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ ተሰኝቷል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከሚሰጣቸው ምቹ የበረራ አገልግሎቶች አንፃር የአንደኛ ደረጃ የሚገባው መሆኑን ከታሪኩ በመነሳት መመስከር እንደሚቻል ‘ቢዝነስ ኢንሳይደር አፍሪካ' በድረ-ገጹ ባሰፈረው ጽህፍ ነው ያስነበበው። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሚሰጣቸው ምቹ፣ ፈጣንና ዘመናዊ አገልግሎቶች የተለያዩ ዓለም አቀፍ የእውቅና ሽልማቶች ተችረውታል። ራም በመባል የሚጠራው የሞሮኮ "ሮያል-ኤየር-ማሮክ" ደግሞ 2ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ፤የደቡብ አፍሪካው "ሳውዝ-አፍሪካን ኤር-ዌይ" ደግሞ 3ኛ ደረጃን የያዘ መሆኑ በዘገባው ተመላክቷል። ኬኒያ-ኤርወይ፣ኤር-ሞሪሽየስ ፣ኢጂብት-ኤር፣ ሩዋንዳ-ኤር፣ የደቡብ አፍሪካ ዓለም አቀፍ መርከብ ድርጅት የሆነው "ሴፍ-ኤር" አየር መንገድ፣ፋስት-ጀት" በሚል የሚጠራው የዚንባቡዌ አየር መንገድ፣ የኤር-ሲሼልስ የተባሉ አየር መንገዶች እንደቅደም ተከተላቸው ከ4ኛ እስከ 10ኛ ያለውን ደረጃን በመያዝ ከአፍሪካ ምርጥ 10 አየር መንገዶች ውስጥ ተካተዋል።
ኢትዮጵያ የምትሳተፍበት የታዳጊ አገራትና የባህር በር የሌላቸው አገራት ከፍተኛ ጉባኤ በኒውዮርክ እየተካሄደ ነው
Sep 23, 2022 384
መስከረም 13 ቀን 2015 (ኢዜአ) በኒውዮርክ እየተካሄደ በሚገኘው 77ኛው የተመድ ጠቅላላ ጉባዔ ጎን ለጎን ኢትዮጵያ ተሳትፎ የምታደርግበት የታዳጊ አገራትና የባህር በር የሌላቸው አገራት ከፍተኛ የምክክር መድረክ በኒውዮርክ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ አገራቱ ችግሮችን በትብብርና በመደጋገፍ መፍታት በሚቻሉባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተዋል። የበለጠ ትብብርን ለማበረታታትና የጋራ ዘላቂ ልማት ለማሳካት የንግድና የትራንስፖርት እንቅፋቶችን ለመቀነስ ቃል የገቡ ሲሆን፤ የቡድኑ አባል ኢትዮጵያ በውይይቱ ንቁ ተሳትፎ እያደረገች ነው። በምክክር መድረኩ ላይ የኢትዮጵያን አቋም ያቀረቡት በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የዓለም አቀፍ ድርጅቶች ዳይሬክተር ጄኔራል አቶ አየለ ሊሬ የባህር በር የሌላቸው አገራት በኮቪድ -19፣ በአየር ንብረት ለውጥ፣ በምግብ፣ በኢነርጂ እና ፋይናንስ ቀውስ እየተፈተኑ ነው ብለዋል። አገራቱ እያጋጠማቸው ያለውን ችግር ለመፍታት ከአሁን በፊት የተቀመጠውን የዶሃ ፕሮግራም ትግበራ ሙሉ በሙሉ ወደ ሥራ ማስገባት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የዶሃ የትግበራ ፕሮግራም ፈጣን ለሆነ ዘላቂና አካታች የማገገሚያና ማቋቋሚያ መንገዶች ትኩረት መስጠቱን ታበረታታለች ነው ያሉት። የዶሃ የትግበራ ፕሮግራም በመተማመንና እውነተኛ ቁርጠኝነት በማሳየት ከልማት አጋሮቻችን ጋር መተግበር ይገባዋል ብለዋል። ኢትዮጵያ በበርካታ ፈተናዎች ውስጥ እያለፈች ቢሆንም ከፍተኛ የፖለቲካ ቁርጠኝነት በማሳየት የ10 ዓመት የልማት ዕቅድ አዘጋጅታ በድህነት ቅነሳ፣ ስራ ፈጠራ፣ መዋቅራዊ ለውጥ፣ ሰላም እና መልካም አስተዳደርን ለማሻሻል እየሰራች መሆኑን ገልፀዋል። የአየር ንብረት ለውጥ እያስከተለ ያለውን ችግር ለመከላከልም ኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብርን በመተግበር 25 ቢሊዮን ችግኞች መተከላቸውን መናገራቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ አመልክቷል።
ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ምርመራ የባለሙያዎች ኮሚሽን ያቀረበውን ሪፖርት በርካታ ሀገራት እንደማይቀበሉት ገለጹ
Sep 22, 2022 367
መስከረም 12 / 2015(ኢዜአ) ዓለም አቀፉ የሰብዓዊ መብት ምርመራ የባለሙያዎች ኮሚሽን ያቀረበውን ሪፖርት በርካታ ሀገራት እንደማይቀበሉት አስታወቁ። 51ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ ምክር ቤት መደበኛ ስብስባውን ከመስከረም 2 ቀን 2015 ዓ.ም በስዊዘርላንድ ጄኔቫ እያካሄደ መሆኑ ይታወቃል። ምክር ቤቱ ዛሬ በ11ኛ ቀን ውሎው በኢትዮጵያ ላይ ላይ አሳታፊ ውይይት (Interactive Dialogue) እያደረገ ይገኛል። በኢትዮጵያ ያለውን የሰብአዊ መብት ሁኔታ እንዲያጣራ የተቋቋመው የዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት የባለሙያዎች ኮሚሽን ሪፖርትንም አዳምጧል። ኮሚሽኑ በኢትዮጵያ የማደርገው ምርመራ ጊዜ ይራዘምልኝ በሚል ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብት ምክር ቤት ጥያቄ ባቀረበበት የጄኔቫው ስብሰባ ላይ ሪፖርቱን አቅርቦ አባል አገራት ተወያይተውበታል። በስብሰባው ላይ የተሳተፉ በርካታ ሀገራት ሪፖርቱ ገለልተኛ አይደለም እንዲሁም ፖለቲካዊ አንድምታ የያዘ ነው ሲሉ አጣጥለውታል። በባለሙያዎች ኮሚሽኑ የቀረበውን የምርመራ ሪፖርት ከተቃወሙ ሀገራት መካከል፤ ቻይና፣ ሩሲያ፣ ኪዩባ፣ ቤላሩስ፣ ሰሜን ኮሪያ፣ ቬንዙዌላ እንዲሁም የአፍሪካ ሀገራት ይገኙበታል። ሩሲያ ባቀረበችው ንግግር የኮሚሽኑ ሪፖርት ፖለቲካዊ ተልዕኮ የተጫነው ነው ያለች ሲሆን ቀደም ሲል በተመድ የሰብዓዊ መብት ከፍተኛ ኮሚሽን እና በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በጋራ ለሰሩት ምርመራ እና ሪፖርት ዕውቅና እንደምትሰጥ ገልጻለች። ኮሚሽኑ ያዘጋጀው ሪፖርት ሙያዊ አካሄድን ያልተከተለ መሆኑን ፖለቲካዊ ተጽዕኖም እንዳለበት ነው ያመለከተችው። በጉባኤው ላይ የተሳተፉ በርካታ ሀገራት ኢትዮጵያ የውስጥ ችግሯን በራሷ መፍታት እንደምትችል በማንሳት ሪፖርቱን እንደማይቀበሉት ገልጸዋል። የኮሚሽኑን ሪፖርት በጥርጣሬ ካዩት ሀገራት መካከል ዴንማርክ አንዷ ስትሆን ኮሚሽኑ ምርመራውን ሲይከናውንም ሆነ ሪፖርቱን ሲያዘጋጅ ከኢትዮጵያ እና ከክልል የስራ ሀላፊዎች ጋር የነበረውን ግንኙነት ግልጽ እንዲያደርግ ጠይቃለች። ደቡብ ሱዳን በበኩሏ ባቀረበችው ንግግር ሪፖርቱ ቀደም ሲል በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እና በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን በጋራ ባከናወኑት የጋራ ምርምራ እና ሪፖርት የተሸፈነ በመሆኑ የተለየ ነገር የለውም ብላለች። የ2022 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብዓዊ መብት ካውንስል የአፍሪካ አባል አገራትን በመወከል ንግግር ያደረገችው ኮትዲቯር በበኩሏ ኮሚሽኑ ከተሰጠው ሀላፊነት በላይ መሄዱን ጠቅሳ ተቃውማለች። የካውንስሉ የአፍሪካ አባል ሀገራት ቤኒን፣ ካሜሩን፣ ኮትዲቯር፣ ኤርትራ፣ ጋቦን፣ ጋምቢያ፣ ሊቢያ፣ ማላዊ፣ ሞሪታኒያ፣ ናሚቢያ፣ ሴኔጋል፣ ሶማሊያና ሱዳንን ያካተተ ነው። የካውንስሉ አባል አገራት በኢትዮጵያ ያለውን ችግር ለመፍታት ሁሉም አካላት በአፍሪካ ህብረት በሚመራው የሰላም አማራጭ ላይ እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል።
ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን የአፍሪካ ሕብረት የሰላም ሂደትን እንደሚደግፉ መግለጻቸው አሸባሪው ህወሓት ጦርነቱን ከመጀመሩ አንስቶ መንግሥት የያዘው አቋም ነው - አምባሳደር ስለሺ በቀለ
Sep 22, 2022 347
መስከረም 12 ቀን 2015 (ኢዜአ) “ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ጆ ባይደን የአፍሪካ ሕብረት የሰላም ሂደትን እንደሚደግፉ የገለጹት ዐሳብ መንግሥት አሸባሪው ህወሓት ጦርነቱን ከመጀመሩ አንስቶ ሲያንጸባርቀው የነበረ ፍላጎት ነው” ሲሉ በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ስለሺ በቀለ ገለጹ። 77ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቅላላ ጉባኤ በድርጅቱ ዋና መቀመጫ ኒው ዮርክ በመካሄድ ላይ ነው። የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ትናንት በጠቅላላ ጉባኤው ላይ ባደረጉት ንግግር በኢትዮጵያ ያለው ግጭት መፍትሔ እንዲያገኝ አገራቸው የአፍሪካ ሕብረትን የሰላም ሂደት ትደግፋለች ብለዋል። በአሜሪካ የኢትዮጵያ አምባሳደር ስለሺ በቀለ የፕሬዝዳንቱ ንግግር አሸባሪው ሕወሓት ጦርነቱን ከጀመረ ጊዜ አንስቶ የኢትዮጵያ መንግስት ከያዘው አቋም ጋር የተጣጣመ መሆኑን በትዊተር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ ገልጸዋል። መንግስት የአፍሪካ ሕብረት የሰላም ጥረት እንዲሳካ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ድጋፍ እንዲያደርግ በተደጋጋሚ ጊዜ መግለጹ ይታወቃል። የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ሙሳ ፋቂ ማህማት በቅርቡ የሕብረቱ የአፍሪካ ቀንድ ልዑክ ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ የኃላፊነት ጊዜ ማራዘማቸው የሚታወስ ነው። የናይጄሪያ የቀድሞ ፕሬዝዳንት የቀጠናው ልዑክ ሆነው የተሾሙት በነሐሴ ወር 2013 ዓ.ም ነበር።
አሸባሪው ሕወሓትን የሚያወግዝና አሜሪካ በሽብር ቡድኑ ላይ እርምጃ እንድትወስድ የሚጠይቅ ሰላማዊ ሰልፍ ዛሬ በዋሺንግተን ዲሲ እየተካሄደ ነው
Sep 18, 2022 372
መስከረም 8 ቀን 2015(ኢዜአ) አሸባሪው ሕወሓት የከፈተውን ጦርነት የሚያወግዝና አሜሪካ በሽብር ቡድኑ ላይ እርምጃ እንድትወስድ የሚጠይቅ ሰላማዊ ሰልፍ በዋሺንግተን ዲሲ በመካሄድ ላይ ነው። ዋይት ሐውስ ፊት ለፊት እየተከናወነ በሚገኘው ሰልፍ ኢትዮጰያውያን፣ኤርትራውያን፣ሶማሊያውያንና ሌሎች የኢትዮጵያ ወዳጆች እየተሳተፉ እንደሚገኝ ኢዜአ ከሰላምና አንድነት ለኢትዮጵያ ማህበር ዲሲ ግብረ ኃይል ያገኘው መረጃ ያመለክታል። ሰላማዊ ሰልፈኞቹ አሸባሪው ሕወሓት በኢትዮጵያ ላይ የከፈተውን ዳግም ወረራ የሚያወግዙና "አሜሪካ የሽብር ቡድኑ እየፈጸመ ያለውን አፍራሽ ድርጊት በማውገዝ ተጠያቂ ማድረግ አለባት፣ዘላቂ ሰላም ለማምጣት ከኢትዮጵያ መንግስት ጎን መቆም ይኖርባታል” የሚሉ መፈክሮችን እያሰሙ ነው። የአሜሪካ መንግስት በኢትዮጵያ፣ በኤርትራና በአጠቃላይ በአፍሪካ ቀንድ የምትከተለውን የተሳሳተ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ ዳግም ልታጤነው እንደሚገባ የሚያሳስቡ መልዕክቶች እየተላለፉ ይገኛል። ሰላማዊ ሰልፉን ሰላምና አንድነት ለኢትዮጵያ ማህበር ዲሲ ግብረ ኃይል በአሜሪካ ከሚገኙ የኢትዮጵያ ኮምዩኒቲ አባላት፣ከተለያዩ ተቋማትና አገር ወዳጆች ጋር በመተባበር እንዳዘጋጀው ተገልጿል::
የአለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር የአለም ምግብ ፕሮግራም ነዳጅ መዘረፍን በዝምታ ማለፋቸው ለአሸባሪው ህወሃት ቡድን ያላቸውን ግልጽ ድጋፍ ያሳያል - አን ጋሪሰን
Sep 2, 2022 375
ነሐሴ 27 ቀን 2014 (ኢዜአ) የአለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም የአለም ምግብ ፕሮግራም ነዳጅ በአሸባሪው ህወሃት መዘረፉን እያወቁ ዝምታን መምረጣቸው ለሽብር ቡድኑ ያላቸውን ድጋፍ በግልፅ ያሳያል ሲሉ የፖለቲካ ሳይንስ ምሁሯ አን ጋሪሰን ገለጹ፡፡ የተባበሩት መንግስታት የዓለም የምግብ ፕሮግራም (WFP) ሃላፊ ዴቪድ ቤስሊ የአሻባሪውን ህወሃት ዘረፋ አሳፋሪና አስደንጋጭ በማለት በይፋዊ የትዊተር ገጻቸው ላይ ማስፈራቸውን ምሁሯ አስታውሰዋል፡፡ ምሁሯ ለግሬይ ዞን ድረ-ገጽ በላኩት ጽሁፍ እንዳመለከቱት፤ አሸባሪው ቡድን የሰላም አማራጭን ትቶ ዳግም ጦርነት መክፈቱን ገልጸዋል፡፡ ቡድኑ የፈጸመው የነዳጅ ዘረፋ በበርካቶች ዘንድ ውግዘት የገጠመው የነውር ድርጊት መሆኑን አመልክተዋል። “የትግራይ ህዝብ በከበባ ውስጥ ሆኖ እርዳታ እየቀረበለት አይደለም” በማለት ጩኸት ሲያሰሙ የነበሩት ዋና ዳይሬክተሩ በነዳጅ ዘረፋው ላይ ግን ምንም እንዳልተፈጠረ በዝምታ ማለፍን መርጠዋል ብለዋል፡፡ የሽብር ቡድኑ ዝርፊያ በትግራይ ክልል የምግብ፤ የማዳበሪያና ሌሎች አስቸኳይ የሰብዓዊ ድጋፎች እንዳይደርሱ የሚያስተጓጉል አሳፋሪ ድርጊት እንደሆነ እየታወቀ ዓለምን በእኩልነትና በገለልተኝነት ይመራሉ የተባሉት ቴድሮስ አድሃኖም ስለዘረፋው እንደማያውቁ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ ዋና ዳይሬክተሩ ህወሃት ከማዕከላዊ ስልጣን በህዝብ ትግል ከተወገደና በሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት ከሰነዘረ በኋላ “በትግራይ ሰብአዊ ቀውስ ተፈጥሯል” በማለት ቅስቀሳ ማድረግን እንደ ዋና ተልዕኮ በመያዝ ቀጥለውበታል ብለዋል። ምሁሯ በአፋርና በአማራ ክልሎች ባደረጓቸው ጉብኝቶች የቡድኑ ወረራ የጎዳቸው ተፈናቃዮች በንጽህና፣ በህክምና፣ በምግብና በውሃ እጥረት ሲንገላቱ መመልከታቸውን አስታውሰዋል። ኢትዮጵያን እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ፤
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም