ዓለም አቀፍ ዜናዎች
በህንድ የአውሮፕላን አደጋ የ204 ዜጎች ህይወት አልፏል- የሕንድ ፖሊስ
Jun 12, 2025 100
አዲስ አበባ፤ሰኔ 5/2017 (ኢዜአ)፦በህንድ የአውሮፕላን አደጋ የ204 ዜጎች ህይወት ማለፉን የሀገሪቷ ፖሊስ አስታወቀ። በሕንድ 242 መንገደኞችን ይዞ በህንድ ሰሜን ምዕራባዊ ክፍል አህመዳባድ ከተማ ከሚገኘው አውሮፕላን ማረፊያ ወደ ለንደን ጋትዊክ ለማምራት በተነሳበት ቅፅበት በአካባቢው በሚገኝ ሆስፒታል የህክምና ባለሙያዎች ማረፊያ ላይ ተከስክሷል። በቦይንግ 787-8 ድሪምላይነር አውሮፕላን ውስጥ 169 ህንዳውያን፣ 53 የብሪታኒያ ዜጎች፣ 7 ፖርቹጋላዊ እና አንድ ካናዳዊ ነበሩ።   በአደጋው የተረፈ ሰው ለማግኘት የሚቻልበት እድል እጅጉን የጠበበ ነው ሲል የአህመዳባድ ፖሊስ ኃላፊ ለአሶሲዬትድ ፕሬስ ገልጾ ነበር። ይሁንና ማምሻውን በወጣ መረጃ የ40 ዓመት የህንድ እና ብሪታኒያዊ ጥምር ዜግነት ያለው ቪሽዋሽ ኩማር ራሜሽ ከአደጋው መትረፉ ተጠቁሟል። እስከ አሁን የ204 ሰዎች አስክሬን ተገኝቷል። የአውሮፕላኑ አካል የህክምና ባለሙያዎች ማረፊያ ላይ ወድቆ ቢያንስ አምስት የህክምና ተማሪዎች መሞታቸውን እና 50 ገደማ የሚሆኑት መጎዳታቸው ተገልጿል። የሕንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት የሀዘን መግለጫ መልዕክት አደጋው ቃል ከሚገልጸው በላይ ልብ የሚሰብር ነው ሲሉ ገልጸዋል። በአደጋው ለተጎዱ በሙሉ ልባዊ ሀዘናቸውን በመግለጽ መጽናናትን ተመኝተዋል።
ኮሚሽኑ በአፍሪካ ሰላምና ደህንነት ማስፈን ዋንኛ የትኩረት አቅጣጫው አድርጎ ይሰራል- መሐሙድ አሊ ዩሱፍ
May 12, 2025 828
አዲስ አበባ፤ግንቦት 4/2017(ኢዜአ)፡- የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን አዲሱ አስተዳደር በአፍሪካ ሰላምና ደህንነት ማስፈን ዋንኛ የፖሊሲ የትኩረት አቅጣጫው በማድረግ እንደሚሰራ የኮሚሽኑ ሊቀ-መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን አዲሱ ሊቀ-መንበር መሐመድ አሊ ዩሱፍ ከሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ጋር ዛሬ ትውውቅ እና ቆይታ አድርገዋል። ሊቀ-መንበሩ በስልጣን ጊዜያቸው ሊያሳኳቸው ስላቀዷቸው ተቋማዊ ግቦችና ቅድሚያ ሰጥተው ለመፈጸም ያሳቧቸውን ስትራቴጂካዊ ጉዳዮች አስመልክቶ ገለጻ አድርገዋል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን አዲሱ አስተዳደር በሰላም፣ ደህንነት፣ ልማትና ዓለም አቀፍ ትብብር ላይ በቁርጠኝነት እንደሚሰራ ገልጸዋል። መሐመድ አሊ ዩሱፍ ሰላምና ደህንነት የኮሚሽኑ ዋንኛ የትኩረት ማዕከል መሆኑን አመልክተዋል። ኢ-ሕገ መንግስታዊ የመንግስት ለውጦች በአፍሪካ መረጋጋት ላይ ከፍተኛ ስጋት መደቀናቸውን ተናግረዋል።   የአፍሪካ ህብረት መሰል ችግሮችን በመፍታት እንዲሁም ሰላምን በማስፈንና የዴሞክራሲ ስርዓትን በማረጋገጥ የህብረቱ አባል ሀገራትን ሉዓላዊነት እና ደህንነት መጠበቅ ላይ አበክሮ ይሰራል ነው ያሉት። ሊቀ-መንበሩ በገለጻቸው ኮሚሽኑ በዓለም አቀፍ መድረክ የአፍሪካን ድምጽ የበለጠ ለማጉላት እንደሚሻ ገልጸዋል። በዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ ውስጥ የአፍሪካ ህብረትን ሚና ማጠናከር ቁልፍ ግብ መሆኑን ጠቅሰው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት ላይ ማሻሻያ እንዲደረግበት በጽኑ ሁኔታ እንደሚሟገት አመልክተዋል። ሊቀ-መንበሩ የፀጥታው ምክር ቤት አሁናዊ መዋቅር የታሪክ ኢ-ፍትሃዊነት በማለት የገለጹት ሲሆን አፍሪካ በዓለም አስተዳደር የሚገባትን ትክክለኛ ስፍራ በሚገልጽ ሁኔታ ምክር ቤቱ ማሻሻያ ሊደርግበት ይገባል ሲሉም ተናግረዋል። በሌላ በኩል በዲጂታል ኢኮኖሚና ሰው ሰራሽ አስተውሎት አማካኝነት በአፍሪካ ፈጠራ እና ዘላቂ ልማትን ማሳለጥ ሌላው የትኩረት አቅጣጫ ነው ብለዋል። የህብረቱ ኮሚሽን ከቀጣናዊ ኢኮኖሚ ማህበረሰቦች ጋር ያለውን ትብብር የበለጠ በማጠናከር ቅንጅታዊ አሰራርን በማጠናከር ወጥነት ባለው መልኩ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ሊቀ-መንበሩ በአፍሪካ በሽታ መከላከልና መቆጣጠር ማዕከል አማካኝነት ወረርሽኝን የመከላከል ዝግጁነት እና ምላሽ አቅም ላይ ከፍተኛ ለውጥ መምጣቱንም አንስተዋል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን አዲሱ ሊቀ-መንበር መሐመድ አሊ ዩሱፍ በቀጣይ ከሀገር ውስጥ እና ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ጋር በየሶስት ወር ጊዜ ቆይታ እንደሚያደርጉ ለማወቅ ተችሏል። በየካቲት ወር 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ በተካሄደው 38ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ መሐመድ አሊ ዩሱፍ ሙሳ ፋቂ ማህማትን በመተካት የኮሚሽኑ ሊቀ-መንበር ሆነው መመረጣቸው የሚታወስ ነው።
ኢትዮጵያ በባንጁል ቻርተር እና በማፑቶ ፕሮቶኮል ያላትን የአፈጻጸም ሪፖርቶች ማቅረብ ጀመረች
May 10, 2025 554
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 2/2017(ኢዜአ)፦ በፍትህ ሚኒስትር ዴኤታ በላይሁን ይርጋ የተመራ የኢትዮጵያ የልዑካን ቡድን በአፍሪካ የሰዎችና ህዝቦች መብቶች ቻርተር ስብሰባ ላይ እየተሳተፈ ነው። በጋምቢያ ባንጁል የአፍሪካ የሰዎችና ህዝቦች መብቶች ኮሚሽን ዋና መሥሪያ ቤት እየተካሔደ ባለው ስብሰባ ላይ በአፍሪካ የሰዎችና ህዝቦች መብቶች ቻርተር (ባንጁል ቻርተር) ወቅታዊ የኢትዮጵያ አፈጻፀምና በአፍሪካ የሴቶች መብቶች ፕሮቶኮል (ማፑቶ ፕሮቶኮል) መነሻ ወቅታዊ አፈጻፀም ላይ ልኡኩ ሪፖርቶችን ማቅረብ ጀምሯል።   ሚኒስትር ዴኤታው ለኢዜአ እንደገለጹት ኢትዮጵያ በሪፖርት ዘመኑ በቻርተሩና ፕሮቶኮሉ መሰረት ያሉባትን ግዴታዎች ለመወጣትና የሰብአዊ መብቶችን ከማስጠበቅ አንጻር የተወሰዱ የፖሊሲ፣ የህግ እና ተቋማዊ እርምጃዎችን የሚመለከቱ ለውጦች ሪፖርት በዝርዝር ቀርቧል። በኮሚሽኑ መርሃ-ግብር መሰረትም ሪፖርቱን ተከትሎ ከኮሚሽነሮች ለተነሱ ጥያቄዎች ኢትዮጵያ በልዑካን ቡድኑ አማካኝነት ሰኞ ግንቦት 4 ቀን 2017 ምላሾችን ትሰጣለች ተብሎ እንደሚጠበቅም ሚኒስትር ዴኤታው ጠቁመዋል። መድረኩ ኢትዮጵያ በባንጁል ቻርተር እና በማፑቶ ፕሮቶኮል ስምምነቶች መሰረት በአገሪቱ የሰብዓዊ መብቶችን እና የፆታ እኩልነትን ለማጎልበት ያላትን ቁርጠኝነት የምታሳይበት እንደሆነም ተገልጿል።
በቱርኪዬ ኢስታንቡል በሬክተር ስኬል 6 ነጥብ 2 የተመዘገበ የመሬት መንቀጥቀጥ ተከሰተ
Apr 23, 2025 1174
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2017(ኢዜአ)፦በዛሬው እለት በቱርኪዬ ኢስታንቡል በሬክተር ስኬል 6 ነጥብ 2 የተመዘገበ የመሬት መንቀጥቀጥ ተከስቷል። እንደ አናዶሉ የዜና ወኪል ዘገባ ዛሬ ቀትር ላይ በተከሰተው የመሬት መንቀጥቀጥ የኢስታንቡል እና ጎረቤት አካባቢ ነዋሪዎች በፍርሃት የመኖሪያ ህንጻቸውን ለቀው እንዲወጡ አድርጓቸዋል። በሌላም በኩል ረፋዱ ላይ በኢስታምቡል አቅራቢያ የባህር ዳርቻ ቡዩኪክሚ የተባለ ስፍራ ላይ በሬክተር ስኬል 4 ነጥብ 9 የተመዘገበ የመሬት መንቀጥቀጥ መከሰቱን አናዶሉ የዜና ወኪል የሃገሪቱን የድንገተኛ አደጋ መቆጣጠር ባለስልጣን ጠቅሶ ዘግቧል። በአደጋው ምንም የተመዘገበ ጉዳት እንዳልተከሰተ የጠቀሰው ዘገባው ነዋሪዎች የዚህ ዓይነት አጠራጣሪ ሁኔታ ሲገጥም የተጎዱ ሕንጻዎች ውስጥ እንዳይገቡ የግድ አስፈላጊ ካልሆነ በስተቀር ተሽከርካሪዎችን እንዳይጠቀሙና ሌሎች የጥንቃቄ መልዕክቶችን ባለስልጣኑ ማስተላለፉም ተገልጿል። የሃገሪቱ ፕሬዝዳንት ረሲፕ ጣይብ ኤርዶጋን ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በቅርበት እየተከታተሉ መሆናቸውንና ለዜጎችም መልካም ሁኔታ እንዲገጥማቸው መመኘታቸው ተገልጿል። ፕሬዝዳንቱ ከሃገሪቱ የድንገተኛ አደጋ መቆጣጠር ባለስልጣንና ከሚመለከታቸው አካላት መረጃዎችን በመቀበል በቅርበት እየተከታተሉ እንደሚገኙም ተገልጿል።
አፍሪካውያን ዓለም አቀፍ ጫናዎችን መቋቋም የሚያስችል አቅም መገንባት ይኖርብናል - የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ
Apr 15, 2025 1235
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2017(ኢዜአ)፦አፍሪካውያን ዓለም አቀፍ ጫናዎችን ለመቋቋም የሚያስችል ሁሉን አቀፍ አቅም መገንባት ይኖርብናል ሲሉ የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር መሀሙድ አሊ ዩሱፍ ገለጹ። የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት 24ኛ አስቸኳይ ስብሰባውን ዛሬ በአዲስ አበባ ማካሄድ ጀምሯል። ምክር ቤቱ በስብሰባው የአፍሪካ ህብረት የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት የአንድ አባል ምርጫ ያካሂዳል ተብሎ ይጠበቃል። በተመሳሳይ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የዓለም አቀፍ ህግ አማካሪ አደረጃጀት (AUCIL) አንድ አባል እንዲሁም የአፍሪካ የህዋ ምክር ቤት (AfSC) አንድ አባል ምርጫ ይከናወናል ። በተጨማሪም ምክር ቤቱ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የኢኮኖሚ ልማት፣ ቱሪዝም፣ ንግድ፣ ኢንዱስትሪ እና ማዕድን ኮሚሽን እና የትምህርት ፣ሳይንስ ፣ ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን ኮሚሽነር የምርጫ ሂደት አስመልክቶ የተዘጋጀ ረቂቅ ሪፖርት ያዳምጣል። የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የአፍሪካ አህጉር በርካታ ውስብስብ ችግሮች እየገጠሙት ይገኛል። የአንዳንድ እርዳታ ሰጭ ተቋማት ድጋፍ መቋረጥ በጤናና በምግብ ዋስትና ላይ ተግዳሮት መፍጠሩን ጠቅሰው፤ አፍሪካውያን ዓለም አቀፍ ጫናዎችን መቋቋም የሚያስችል ሁሉን አቀፍ አህጉራዊ ነጻ የንግድ ቀጣና የመሳሰሉ ዘዴዎችን ለመተግበር በትኩረት መስራት እንደሚገባቸው ጠቁመዋል። የአንጎላ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና የወቅቱ የምክር ቤቱ ሊቀ-መንበር ቴቴ አንቶኒዮ በበኩላቸው፤ ሰላም እና መረጋጋት ለእድገት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። አህጉራዊ ተቋማት የሰላም እና የጸጥታ ጉዳዮችን ለመቋቋም የሚያስችል ጠቃሚ ግብዓት እንዳላቸው ጠቁመው፤ ይህም የውሳኔ ሰጭውን አካል መፍትሄ የሚፈለግ መሆኑን ተናግረዋል። የአፍሪካ ህብረት እነዚህን ተግዳሮቶች በጥበብ እና አርቆ አስተዋይ አመራር በመምራት ረገድ ንቁ መሆን አለበት ያሉት ደግሞ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ተወካይ አምባሳደር ሒሩት ዘመነ ናቸው። የ2063 አጀንዳን ራዕይ ለማሳካትና የበለፀገች አህጉርን ለመፍጠር አህጉራዊ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ ቀልጣፋ ስራ መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የምክር ቤቱ አስቸኳይ ስብስባ እየተካሄደ ያለው በየካቲት 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ በተደረገው 38ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ በተላለፈው ውሳኔ መሰረት ነው።  
ስድስተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ውይይት እና የዘላቂ ልማት ግቦች ፎረም ተጀመረ
Apr 7, 2025 785
አዲስ አበባ፤መጋቢት 29/2017(ኢዜአ)፦ ስድስተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ውይይት እና የዘላቂ ልማት ግቦች ፎረም ዛሬ በዩጋንዳ ካምፓላ መካሄድ ጀምሯል። ውይይቱ እየተካሄደ የሚገኘው “ የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል እርምጃዎችን በፋይናንስ መደገፍ ለአፍሪካ ዘላቂ አረንጓዴ እድገት እና ልማት፤ የፍትህ ጉዳይ” በሚል መሪ ሀሳብ ነው። በመክፈቻው ላይ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የግብርና፣ ገጠር ልማት፣ ብሉ ኢኮኖሚ እና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽነር ሞሰስ ቪላካቲ፣ የህብረቱ አመራሮች፣ የአፍሪካ ሀገራት ተወካዮች፣ ፖሊሲ አውጪዎች፣ ተመራማሪዎች፣ አጋሮች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። በአዘርባጃን ባኩ የተካሄደው 29ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ 29) የተላለፉ ውሳኔዎች በአፍሪካ ላይ የሚኖራቸውን አንድምታ በተመለከተ ምክክር እንደሚደረግ ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው ያመለክታል። በኮፕ 29 ላይ የአየር ንብረት ለውጥ ፋይናንስ አስመልክቶ ውሳኔ የተደረሰባቸው ጉዳዮች ለአፍሪካ ጥያቄ አጥጋቢ ምላሽ አለመስጠታቸውን የገለጸው ህብረቱ በጉዳዩ ሀገራት ድምጻቸውን እንደሚያሰሙ ገልጿል። በብራዚል ቤለም በቀጣዩ ዓመት በሚካሄደው 30ኛው የተባበሩት መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ጉባዔ (ኮፕ 30) የአፍሪካ የጋራ አቋም ምን መሆን አለበት? በሚለው ጉዳይ ውይይት እንደሚደረግ ይጠበቃል። እ.አ.አ በ2024 አፍሪካን የተመለከቱ የአየር ንብረት ለውጥ ጉዳዮች እና በ2025 በሚኖሩ አጀንዳዎች ላይም ምክክር ይደረጋል። በአዲስ አበባ በተካሄደው 38ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ እና የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች እና መንግስታት የአየር ንብረት ለውጥ ኮሚቴ (CAHOSCC ) በአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ያሳለፏቸው ውሳኔዎች ይገመገማሉ። የአፍሪካ የዘላቂ ልማት ግቦች አፈጻጸም እና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎችም ሌላኛው የውይይቱ አጀንዳ ናቸው። በንጹህ መጠጥ ውሃ እና በማህበረሰብ ጤና አጠባበቅ ላይ ትኩረቱን ያደረገው የዋሽ ፕሮጀክት (WASH) አፈጻጸም ለተሳታፊዎች ቀርቦ ምከረ ሀሳብ ይሰጥበታል። በስብሰባው የአየር ንብረት ለውጥ መከላከል እና የዘላቂ ልማት ግቦችን የተመለከተ የውሳኔ ሀሳብ እንደሚጸድቅ የህብረቱ መረጃ ያመለክታል። ስድስተኛው የአፍሪካ የአየር ንብረት ውይይት እና የዘላቂ ልማት ግቦች ፎረም እስከ ነገ ይቆያል።  
የአፍሪካ የውቅያኖስ አስተዳደር ስትራቴጂ ወደ ትግበራ ሊገባ ነው 
Mar 31, 2025 765
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 22/2017(ኢዜአ)፡- የአፍሪካን የባህር እና የመጠጥ ውሃ ሀብቶች ያለውን ቀጣናዊ ትብብር ማጠናከርን ያለመው የአፍሪካ የውቅያኖስ አስተዳደር ስትራቴጂ ወደ ትግበራ ሊገባ መሆኑ ተገለጸ። ስትራቴጂውን ለማፅደቅ የተዘጋጀ አውደ ጥናት ከነገ ጀምሮ በታንዛንያ ዳሬ ሰላም ይካሄዳል። ስብሰባውን ያዘጋጁት የአፍሪካ ህብረት እና የተባበሩት መንግስታት የአካባቢ ጥበቃ ፕሮግራም በጋራ በመተባበር ነው። የአፍሪካ የውቅያኖስ አስተዳደር ስትራቴጂ የአፍሪካን የባህር እና የመጠጥ ውሃ ሀብቶች የሀገራት እና የዘርፉ ተዋንያን ትብብርን ለማጠናከር ያለውን ፋይዳ አስመልክቶ ውይይት እንደሚደረግ ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል። የስትራቴጂው ተቋማዊ ማዕቀፍ፣ የክትትል ስርዓትና የድርጊት መርሃ ግብር ውይይት የሚደረግባቸው ዋነኛ አጀንዳዎች ናቸው። የአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት ስትራቴጂውን ከብሄራዊ እቅዶቻቸው ጋር አጣጥመው በሚተገብሩበት ሁኔታ ላይም ይመክራሉ። የውቅያኖስ አስተዳደር ስትራቴጂው ከአፍሪካ የብሉ ኢኮኖሚ ስትራቴጂ፣ ከዘላቂ ልማት እና ዓለም አቀፍ ግቦች ጋር ያለው ትስስርም ውይይት ይደረግበታል። እ.አ.አ በ2023 በአሜሪካ ኒው ዮርክ የተፈረመው ዓለም አቀፍ የባህር ብዝሃ ህይወት ዘላቂ አጠቃቀም ስምምነት (BBNJ Agreement) የትግበራ አፈጻጸም ሌላው የአውደ ጥናቱ የመወያያ አጀንዳ ነው። የአፍሪካ ሀገራት እ.አ.አ ጁን 2025 በፈረንሳይ ኒስ በሚካሄደው ሶስተኛው የተባበሩት መንግስታት የውቅያኖስ ኮንፍረንስ ላይ ይዘው የሚቀርቡትን የጋራ አቋም ይፋ እንደሚያደርጉም የህብረቱ መረጃ ያመለክታል። የአፍሪካ የውቅያኖስ አስተዳደር ስትራቴጂ ለማፅደቅ የሚደረገው አውደ ጥናት እስከ መጋቢት 26 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል።
የአፍሪካ ነጻ ንግድ ቀጣና ስምምነትን በማጽደቅ 48 ሃገራት ቁርጠኝነታቸውን አሳይተዋል
Mar 25, 2025 419
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያን ጨምሮ እስካሁን 48 ሀገራት የአፍሪካ ነጻ ንግድ ቀጣና ስምምነትን በማጽደቅ ለትግበራው ቁርጠኛነታቸውን ማሳየታቸውን የአህጉራዊ ነጻ ንግድ ቀጣናው ዋና ጸሐፊ ዋምኬሌ ሜኔ ገለጹ። የአፍሪካ አህጉራዊ ነጻ ንግድ ቀጣና በአፍሪካ አጀንዳ 2063 የልማት ማዕቀፍ ከተያዙ ግዙፍ አህጉራዊ ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ ሲሆን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎችን ስር ከሰደደ ድህነት እንደሚያላቅቅ ይጠበቃል። የአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት መሪዎች አህጉራዊ የነጻ ንግድ ቀጣና መመስረቻ ስምምነትን እ.ኤ.አ. በ2018 በሩዋንዳ ዋና ከተማ ኪጋሊ መፈረማቸው ይታወቃል። ኢትዮጵያም ስምምነቱን በወቅቱ ከመፈረም ባለፈ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በኩል መጋቢት 12/2011 ዓ.ም አፅድቃለች። ዋና ጸሐፊው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አህጉራዊ የነጻ ንግድ ቀጣና ስምምነቱን 48 የአህጉሪቱ አባል ሀገራት አጽድቀውታል። እነዚህ ሀገራት ስምምነቱን ለመተግበር ያላቸውን ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት ማሳየታቸውን ጠቅሰው፤ አህጉራዊ የኢኮኖሚ ውህደትን የሚያሳልጡ ጠንካራ የህግ ማዕቀፎች እያዘጋጁ ነው ብለዋል። ከዚህም ባለፈ 19 አባል ሀገራት የቀረጥ መርሃ ግብር በማውጣት የንግድ ግብይት ለመፍጠር መዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል። አክለውም የአነስተኛና መካከለኛ አርሶ አደሮችን ምርት በማሰባሰብ አህጉራዊ የንግድ ትስስርን የሚያጠናክሩ ድርጅቶችን ለማቋቋም ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የንግድ ድርጅቶችን ለማቋቋም በሚደረገው ጥረትም የአፍሪ-ኢግዚም ባንክ ለነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነቱ የ750 ሚሊዮን ዶላር ገንዘብ ድጋፍ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆኑንም አስረድተዋል። የአፍሪካን የኢኮኖሚ ውህደትና ዕድገት በማረጋገጥ የህዝቧን ተጠቃሚነት ማጎልበት የህልውና ጉዳይ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የቀድሞ የናይጄሪያ ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር ዬሚ ኦሲንባጆ ናቸው። የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነትን በጠንካራ የፖለቲካ አመራር መተግበር የአህጉሪቱን የኢኮኖሚ ውህደት ለማፋጠን ቁልፍ ጉዳይ መሆኑንም ተናግረዋል። ከአህጉራዊ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክት መካከል አንዱ የሆነው ነጻ የንግድ ቀጣና ስምምነቱ፤ የአፍሪካን የወደፊት የኢኮኖሚ እጣ ፋንታ የሚወስን መሆኑንም ተናግረዋል። የአፍሪካ የኢኮኖሚ ውህደትና ዕድገት የህዝቦችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ የህልውና ጉዳይ ተደርጎ መታየት እንዳለበት ጠቅሰው፤ ለስኬቱም ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት ወሳኝ ነው ብለዋል። የአፍሪካን አህጉራዊ ውህደት ራዕይን እውን ለማድረግ እ.ኤ.አ በ1963 ከአፍሪካ አንድነት ድርጅት መቋቋም ጀምሮ የተለያዩ ጥረቶች ተደርገዋል። ለአብነትም የአፍሪካ መሪዎች እ.አ.አ በ2012 በአዲስ አበባ በተካሄደው የህብረቱ 18ኛ መደበኛ ጉባኤ አህጉራዊ የነጻ ንግድ ቀጣና እንዲመሰረት ውሳኔ ማሳለፋቸው ይታወቃል። ይህንን ተከትሎም እ.ኤ.አ በ2015 ድርድሩን በይፋ በመጀመር በ2018 አህጉራዊ የነጻ ንግድ ቀጣና መመስረቻ ስምምነቱ በይፋ ተፈርሟል። የአፍሪካ የነጻ ንግድ ቀጣና ስምምነት 55 የአፍሪካ ሀገሮችን በአንድነት ያካተተ የነጻ ንግድ ስርዓት የፈጠረ በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነ ስምምነት ነው፡፡ የአፍሪካ ሀገራት በአብዛኛው እቃዎች ላይ በሂደት ታሪፍን ለማስወገድ፣ የአገልግሎት ንግድን በሂደት ክፍት ለማድረግ እና የንግድ መሰናክሎችን ለማስወገድ የተስማሙበትም ነው፡፡
ኢጋድ በደቡብ ሱዳን ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት እንዲሰፍን በቁርጠኝነት ይሰራል - ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር)
Mar 14, 2025 379
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 5/2017(ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) በደቡብ ሱዳን ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት እንዲሰፍን ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን በቁርጠኝነት እንደሚሰራ የተቋሙ ዋና ጸሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) ገለጹ። ዋና ፀሐፊው ከወቅቱ የኢጋድ ሊቀ መንበር እና የጅቡቲ ፕሬዝዳንት ኢስማኤል ኦማር ጌሌ ጋር ተወያይተዋል። ውይይቱ የደቡብ ሱዳን ወቅታዊ ሁኔታ አስመልክቶ ከትናንት በስቲያ በተካሄደው 43ኛው የኢጋድ አስቸኳይ የመሪዎች ጉባኤ ውጤቶች ላይ ያተኮረ ነበር።   ዋና ጸሀፊው ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) በውይይቱ በጉባዔው ላይ የተላለፉ ውሳኔዎች ተግባራዊነት እና ኢጋድ ቀጣናዊ ፈተናዎችን ለመፍታት ያለው ቁርጠኝነት ላይ ከሊቀመንበሩ ጋር ሀሳቦች እንደተለዋወጡ በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል። ኢጋድ በደቡብ ሱዳን ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት እንዲሰፍን ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን በሙሉ ቁርጠኝነት እንደሚሰራ አመልክተዋል። አስቸኳይ ጉባኤውን ተከትሎ የደቡብ ሱዳን ኃይሎች አለመግባባቶችን በውይይት እና በሰላማዊ መንገድ ብቻ እንዲፈቱ ኢጋድ ጥሪ ማቅረቡ ይታወሳል።
ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት የአፍሪካን ፍትሐዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጥ መልኩ መሻሻል አለባቸው
Feb 12, 2025 702
አዲስ አበባ፤ የካቲት 5/2017(ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት የአፍሪካን ፍትሐዊ ተጠቃሚነት በሚያረጋግጥ መልኩ መሻሻል እንዳለባቸው በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ፀሐፊ ክላቨር ጋቴቴ ገለጹ። 46ኛው የአፍሪካ ህብረት አባል ሀገራት የስራ አስፈፃሚዎች ምክር ቤት ስብሰባ በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ እየተካሔደ ይገኛል። በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ዋና ፀሐፊ ክላቨር ጋቴቴ በዚህ ወቅት፤ አፍሪካውያን የተፈጥሮ ሀብታቸውን በአግባቡ መጠቀም አልቻሉም ብለዋል። አፍሪካ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ የምታሳድረው ተፅዕኖ ጥቂት ቢሆንም የጉዳቱ ገፈት ቀማሽ መሆኗን ገልጸዋል። በመሆኑም የዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት የአፍሪካን ጥቅም በሚያስከብር መልኩ ሪፎርም መደረግ አለባቸው ብለዋል። የዓለም አቀፉ የፋይናንስ ስርዓት በመሰረታዊነት መቀየር እንዳለበትም ገልጸዋል። አፍሪካውያን አህጉራዊ ሀብታቸውን እሴት ጨምረው መጠቀም እንዲችሉ የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። በአህጉሪቱ ጥሬ ምርትን ወደ ውጭ ከመላክ ይልቅ በምርቶች ላይ እሴትን ጨምሮ የመላክ አቅምን ማጠናከር እንደሚገባ ተናግረዋል። አፍሪካውያን ለደረሰባቸው ግፍና በደል ተገቢ የፍትሕ ካሳ ሊያገኙ እንደሚገባም ገልጸዋል። ይህ ችግር የዓለም የንግድ ስርዓትን በማዛባት የአፍሪካውያንን ፍትሀዊ ተጠቃሚነት በእጅጉ የጎዳ መሆኑን ተናግረዋል። አፍሪካ አየር ንብረት ለውጥ ላይ ያላት አሉታዊ ተፅዕኖ ውስን ቢሆንም የጉዳቱ ሰለባ ከመሆን አልዳነችም ብለዋል። የአየር ንብረት ለውጥ ተፅዕኖ አፍሪካን የአህጉራዊ ጥቅል ምርቷን አምስት በመቶ እንደሚያሳጣት በመጥቀስ፣ በዓለም ዙሪያ ለኢንቨስትመንት ከሚመደበው ሀብት የአፍሪካ ሁለት በመቶ ብቻ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ይሄ የአፍሪካን ጥቅም የሚጎዳ ኢፍትሃዊነት በቃህ ሊባል ይገባል ብለዋል። ለዚህ ደግሞ የዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት መሰረታዊ ሪፎርም ሊደረግባቸው እንደሚገባ ገልጸዋል።  
የቀድሞው ሴናተር ቦብ ሜኔንዴዝ የ11 ዓመት እስራት ተፈረደባቸው
Jan 30, 2025 589
አዲስ አበባ፤ ጥር 22/2017(ኢዜአ)፦ ከታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ጋር ተያይዞ በሙስና በመደለል ከግብፅ መንግስት ጉቦ የተቀበሉት አሜሪካዊው የቀድሞው የኒው ጀርዚ ሴናተር ቦብ ሜኔንዴዝ የ11 ዓመት እስራት ተፈርዶባቸዋል። በኒው ዮርክ በ12 ዳኞች የተሰየመው ችሎት የፍርድ ውሳኔውን ትናንት ማስተላለፉን የአሜሪካው የቴሌቪዥን ጣቢያ ኤንቢሲ ዘግቧል። ችሎቱ ከዚህ ቀደም የ71 ዓመቱን የሕግ ባለሙያና ፖለቲከኛ በ16ቱም የሙስና ወንጀሎች ጥፋተኛ ብሏቸዋል። የአሜሪካ ፌደራል ዐቃቤ ሕጎች የቀድሞውን ሴናተር ጉቦ ተቀብለው የግብጽ ወኪል ሆኖ በመስራት፣ ፍትሕ እንዲዛባ በማድረግና የማይገባ ጥቅም ለማግኘት ወንጀል መክሰሳቸው ይታወቃል። ዐቃቤ ሕጉ ሜኔንዴዝ የአሜሪካ ሴኔት የውጭ ጉዳዮች ኮሚቴ ሰብሳቢ በነበሩበት ወቅት የግብጽን ፍላጎት በማንጸባረቅ፣ ለዚህም ከግብጽ መንግስት ገንዘብ ማግኘታቸው በሰነድና በሰው ማስረጃ አረጋግጧል። የቀድሞው ሴናተር በታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ጋር በተገናኘ በኢትዮጵያ ላይ ጫና እንዲደረግ በኒው ጄርሲ በንግድ ስራ ላይ ከተሰማሩ 3 የግብጽ ሰዎች እጅ ወርቅ እና ጥሬ ገንዘብ ጉቦ ተቀብለዋል። ይህም ሴናተሩ ራሳቸውን ለግብጽ መንግሥት ወኪል አድርገው በመቆም ሰርተዋል የሚል ክስ ሲቀርብባቸው እንደነበረ ይታወቃል። በዚህም በዘረፋ፣ ጉቦ በመቀበል፣ ስልጣንን አላግባብ በመጠቀም፣ በሴራ፣ ፍትህን በማደናቀፍና መሰል 16 ወንጀሎች ላይ ተሳትፎ ማድረጋቸው ተገልጿል። በ16 የሙስና ወንጀሎች ጥፋተኛ የተባሉት ሜኔንዴዝ የግብፅ መንግስት በሚሊዮን ዶላሮች የሚገመት የአሜሪካ መንግስት ወታደራዊ ድጋፍ እንዲያገኝ ረድተዋል የሚል ክስ እንደቀረባበቸውም እንዲሁ። ሜኔንዴዝ የውጪ መንግስታትን ፍላጎት ለማስፈጸም ከተቀበሏቸው ስጦታዎች መካከል 100 ሺህ ዶላር የሚያወጣ ወርቅና ቅንጡ መርሰዲስ መኪና የተጠቀሱ ሲሆን፣ በመኖሪያ ቤታቸውም 480 ሺህ ዶላር ጥሬ ገንዘብ በቤታቸው መገኘቱን የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ከዚህ ቀደም በስፋት ዘግበውታል። የቀድሞው ሴናተር ከግብጽ የንግድ ባለቤቶች ጋር የጥቅም ትስስር እንደነበራቸው ተጠቁሟል። በክሳቸው ላይ ከግብጽ በተጨማሪ ከሌሎች የውጭ መንግስታት ጉቦ መቀበላቸው በምርምራ እንደተረጋገጠም ተመላክቷል። እ.አ.አ በ2021 የ‘ኢትዮጵያ ስታብላይዜሽን ፒስ ኤንድ ዴሞክራሲ አክት’ ወይም ኤች አር 6600 ረቂቅ ሕግ ተጓዳኝ ወይም አጋዥ (ኮምፓኒየን ቢል) የሆነው የኢትዮጵያ ፒስ ኤንድ ዴሞክራሲ ፕሮሞሽን አክት ኦፍ 2022’ ወይም ‘ኤስ.3199’ የተዘጋጀው በ70 ዓመቱ ፖለቲከኛና የሕግ ባለሙያ ቦብ ሜኔንዴዝ ዋና አርቃቂነት ነው። በአሜሪካ የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያውያን ረቂቅ ሕጎቹ በሕግ አውጪው አካል ድምጽ ተሰጥቶባቸው እንዳይጸድቁ ለማድረግ ሴናተሮችና የኮንግረስ አባላትን በማናገር፣ደብዳቤ በመጻፍ፣ፊርማ በማሰባሰብና በማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ዘመቻ በማድረግ ጥረት አድርገዋል። ሕጉ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅምና ፍላጎት የሚጎዳና ሉዓላዊነቷን የሚጥስ እንደነበር በተደጋጋሚ ጊዜ ሲገለጽ ቆይቷል። እነዚህ ሕጎች እንዲፀድቁ ግብጽ ግፊት ስታደርግ እንደነበር ይታወቃል።
አሜሪካ ከዓለም ጤና ድርጅት አባልነት የመውጣቷን ውሳኔ ማጤን አለባት - የአፍሪካ ህብረት
Jan 22, 2025 683
አዲስ አበባ፤ ጥር 14/2017(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር ሙሳ ፋኪ ማሃማት አሜሪካ ከዓለም ጤና ድርጅት አባልነት የመውጣት ውሳኔዋን እንድታጤነው ጠይቀዋል፡፡ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ ማሃማት ጉዳዩን አስመልክተው መግለጫ አውጥተዋል። በመግለጫቸውም አሜሪካ ከድርጅቱ አባልነት ለመውጣት መፈለጓ እንዳሳዘናቸው ሙሳ ፋኪ ገልጸዋል። ውሳኔውን መለስ ብሎ በማጤን በአባልነቷ ትቀጥላለች የሚል ተስፋ እንዳላቸውም አስታውቀዋል። አሜሪካ የአፍሪካ የበሽታ መቆጣጠሪያና መከላከል ማዕከል(አፍሪካ ሲዲሲ) መስረታ ላይ ቀደምት እና ጠንካራ ደጋፊ ነበረች ሲሉም በመግለጫቸው አስታውሰዋል፡፡ አሁን ላይ ከመቼውም ጊዜ በላይ ዓለም አቀፉን የህብረተሰብ ጤና ደህንነት እንደ አንድ የጋራ ጥቅም የማረጋገጥ ተልዕኮውን ለመወጣት በዓለም ጤና ድርጅት ላይ ጥገኛ መሆኑን የገለፀው ህብረቱ፤ የድርጅቱ ቁልፍ መስራች አባል የሆነችው አሜሪካ ከተቋሙ የመውጣት ውሳኔዋን በድጋሚ እንድታጤነው ጠይቋል።
26ኛውን የዓለም የእንስሳት ጤና ድርጅት የአፍሪካ አህጉራዊ ጉባኤን ኢትዮጵያ ታዘጋጃለች - ግብርና ሚኒስቴር  
Jan 15, 2025 630
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ 26ኛውን የዓለም የእንስሳት ጤና ድርጅት የአፍሪካ አህጉራዊ ጉባኤ ልታስተናግድ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። የዓለም የእንስሳት ጤና ድርጅት ጉባኤ በየዓመቱ በግንቦት ወር በፈረንሳይ ፓሪስ የሚካሄድ ሲሆን በየሁለት ዓመቱ ደግሞ በየአህጉራቱ እንደሚካሄድ ሚኒስቴሩ ገልጿል፡፡ በአፍሪካ ደረጃ 25ኛው ጉባኤ እአአ በ2023 ቦትስዋና ያስተናገደች ሲሆን 26ኛውን ጉባኤ ኢትዮጵያ እንድታዘጋጅ መመረጧንም አስታውቋል። ጉባኤው "የእንስሳት ጤና ለምግብና ስነ-ምግብ ዋስትና መረጋገጥ እና ለሕብረተሰብ ጤና" በሚል መሪ ሀሳብ ከጥር 27 እስከ 30/2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ይካሄዳል፡፡ ለጉባኤው መሳካት ከዓለም የእንስሳት ጤና ድርጅት ዋናው ጽህፈት ቤት፣ የአፍሪካ እና የምስራቅ አፍሪካ ተወካዮች ጋር የተለያዩ ቅድመ ዝግጅቶች ሲደረጉ መቆየታቸውም ተገልጿል። የግብርና ሚኒስቴርም ግብረ-ሃይል በማቋቋም ቅድመ ዝግጅቶች እየተደረጉ መሆኑን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡ በጉባኤው ከየአፍካ ሀገራት የጤና ኃላፊዎችና ቋሚ ተወካዮች፣ ከዓለም የእንስሳት ጤና ድርጅት፣ በየአህጉሩ ያሉ የእንስሳት ጤና አመራሮች፣ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች፣ የልማት አጋሮች፣ የግሉ ዘርፍና የመንግሥት ተቋማት ተወካዮች እንደሚታደሙም ተጠቁሟል። የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ፍቅሩ ረጋሳ(ዶ/ር) በጉባኤው በአፍሪካ የእንስሳት ጤና አገልግሎት፣ ድንበር ዘለል የእንስሳት በሽታዎችን መቆጣጠርና መከላከል በሚቻልበት ሁኔታ ብሎም ከበሽታ ነጻ የሆነ አህጉር ለመፍጠር የሚረዱ ውይይቶች ይደረጋሉ ብለዋል። በጉባኤው በእንስሳት ጤናና ልማት፣ በምግብና ስነ-ምግብ ዙሪያ የሚሰሩ ዓለም አቀፍ ተቋማት እንደሚገኙና የተለያዩ ውሳኔዎች እንደሚተላለፉበት ገልጸዋል። በሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር እየተሰሩ ያሉ እንደ ዝርያ ማሻሻል፣ መኖ፣ የእንስሳት ጤና እና የሕብረተሰብ ጤና አጠባበቅ በስፋት ውይይት ይደረግባቸዋል፤ አቅጣጫዎች ይቀመጡበታል ሲሉም ተናግረዋል። የእንስሳት ጤና በንጥረ ነገር የበለጸገ ምግብ ለማምረት እንደሚረዳ፣ መቀንጨርን ከመከላከል አንጻር የእንስሳት ጤና ምን ያህል አስተዋጽኦ እንዳለውም የምናይበት መድረክ ነው ሲሉም ገልጸዋል። ጉባኤው ኢትዮጵያ ከጎረቤት ሀገራትና በአህጉር ደረጃ ካሉ ሀገራት ጋር ድንበር ዘለል የእንስሳት በሽታዎችን ለመቆጣጠር፣ የገበያ ተደራሽነትን ለማስፋት ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋልም ብለዋል። ሀገራት ያላቸውን የእንስሳት በሽታ መከላከልና መቆጣጠር ስትራቴጂና ተሞክሮ፣ ኢትዮጵያም በእንስሳት ጤና፣ መሰረተ ልማት እና ያሉ መልካም አጋጣሚዎችን ለዓለም የምታስተዋውቅበት፣ ልምድ የምንጋራበት መድረክ ነው ሲሉም ሚኒስትር ዴኤታው ተናግረዋል። ከመቶ ዓመት የዘለለ የእንስሳት ጤና አገልግሎትና የምርምር ተቋማት፣ በእንስሳት ጤና ላይ ትኩረት አድርገው የሚሰሩ፣ ክትባትና መድሃኒት የሚያመርቱ፣ በእንስሳት ጤና የሰው ሃይል የሚያፈሩ ተቋማት መኖራቸው መልካም አጋጣሚዎች መሆናቸውንም ገልጸዋል። በኢትዮጵያ የሚካሄደው የዓለም የእንስሳት ጤና ድርጅት የአፍሪካ ጉባኤ የእንስሳት ጤና እንዲጠበቅ ብሎም ዘርፉ እንዲነቃቃ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ማለታቸውም በመረጃው ተመላክቷል።
የአሜሪካ 39ኛ ፕሬዝዳንት ጂሚ ካርተር በ100 ዓመታቸው አረፉ
Dec 30, 2024 1280
አዲስ አበባ፤ ታኅሳስ 21/2017 (ኢዜአ)፡- የአሜሪካ 39ኛው ፕሬዝዳንት የነበሩት ጂሚ ካርተር በ100 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ። የቀድሞ ፕሬዝዳንቱ በመጨረሻው ጊዜያቸው በፔሊንስ ጆርጂያ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው “በቤተሰቦቻቸው ተከበው ነበር” ሲል ካርተር ሴንተር በሰጠው መግለጫ አስታውቋል። ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን ካርተርን “ውድ ጓደኛ” እና “ልዩ መሪ” ሲሉ የተሰማቸውን ሀዘን አስመልክተው በሰጡት መግለጫ ገልጸዋል። ተመራጩ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው አሜሪካውያን ለቀድሞው ፕሬዝዳንት “የምስጋና እዳ አለባቸው” ብለዋል። የአሜሪካ መንግሥት የቀድሞ ፕሬዝዳንቱን ሥርዓተ ቀብር ለመፈጸም ዝግጅት እያደረገ ስለመሆኑ የሲ.ኤን.ኤን ዘገባ አመልክቷል። የቀድሞ ፕሬዝዳንት ጂሚ ካርተር ባለቤት ሮዛሊን ካርተር እ.ኤ.አ. በ2023 ወርሃ ኅዳር በ96 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል። ሁለቱ ጥንዶች ለ75 ዓመታት አብረው በትዳር አብረው ኖረዋል። ካርተር እ.ኤ.አ. ከ1977 እስከ 1981 አሜሪካን በፕሬዝዳንትነት መርተዋል። ፕሬዝዳንት ካርተር እ.ኤ.አ. በ1980 በተካሄደው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ የካሊፎርኒያ ገዢ በነበሩት ሮናልድ ሬገን ሲሸነፉ የካርተር ማእከልን እ.ኤ.አ. በ1982 አቋቁመው ወደ በጎ አድራጎት ተግባር ተሰማርተው ነበር። የካርተር ማእከልም ከኢትዮጵያ ጋር በሽታን በከላከልና በመቆጣጠር፣ የምግብ ምርትን በማሳደግ፣ ግጭትን በማስወገድና በምርጫ ታዛቢነት በመሳተፍ የረጅም ጊዜ ግንኙነት ነበረው።
ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ተሸፍኗል- ሚኒስቴሩ
Dec 24, 2024 1136
ደሴ፤ ታኅሣሥ 15/2017 (ኢዜአ)፦ በአገር አቀፍ ደረጃ ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር በላይ መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት መሸፈኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለስ መኮንን(ዶ/ር)ን ጨምሮ ከፍተኛ የፌዴራልና የክልል የመንግስት የስራ ሃላፊዎች በተገኙበት በደቡብ ወሎ ዞን ቃሉ ወረዳ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ተጀምሯል። ሚኒስትር ዴኤታው በዚሁ ወቅት እንዳሉት የበጋ መስኖ ስንዴ ምርታማነትን በማሳደግ የዜጎችን የምግብ ዋስትና ከማረጋገጥ ባለፈ ምርት በስፋት ለገበያ ለማቅረብ እየተሰራ ነው፡፡ የውሃ አማራጮችን በመጠቀም ለበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ትኩረት መስጠቱን ጠቁመው፤ በዘንድሮው የበጋ ወራት ከ4 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር መሬት በላይ በስንዴ ለማልማት እየተሰራ ይገኛል፡፡ እስካሁን በተደረገ እንቅስቃሴም ከ2 ነጥብ 4 ሚሊዮን ሄክታር የሚበልጥ መሬት በስንዴ ዘር መሸፈን እንደተቻለ ነው የተናገሩት። ምርታማነትን ለማሳደግ የሚያግዙ ማዳበሪያን ጨምሮ ሌሎች ግብዓቶችን በበቂ መጠን እያቀረበ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡ በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአማራ ክልል ገጠር ልማት ዘርፍ አስተባባሪና ግብርና ቢሮ ኃላፊ ድረስ ሳህሉ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የበጋ መስኖ ስንዴ ልማትን ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም 254 ሺህ ሄክታር መሬት በበጋ መስኖ ስንዴ በማልማት ከ9 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለመሰብሰብ መታቀዱን ገልፀዋል፡፡ እስካሁን ከ120 ሺህ ሄክታር የሚበልጥ መሬት በዘር መሸፈኑን ጠቁመዋል። በክልሉ በተሻሻለ አሰራር ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን ከመቻል ባለፈ በቂ ምርት ለገበያ እንዲቀርብ ጭምር እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡
በአፍሪካ ህብረት ጉባዔ የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ ለመገንባት ዝግጅት አድርገናል -በጎ ፍቃደኞች
Dec 22, 2024 576
አዲስ አበባ፤ታህሳስ 13/2017(ኢዜአ)፦በ38ኛው የአፍሪካ ህብረት ጉባዔ የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ ለመገንባት ዝግጁ መሆናቸውን በጎ ፍቃደኞች ገለጹ። ኢትዮጵያ 38ኛውን የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ በሰለጠነ የሰው ኃይል በመታገዝ በብቃት ለማስተናገድ በቂ ዝግጅት ማድረጓን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ማስታወቁ ይታወሳል። ኢትዮጵያ የህብረቱ መቀመጫና የአፍሪካ መዲና እንደመሆኗ ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ ለማስተናገድ በሁሉም መስክ ቅድመ ዝግጅት ማጠናቀቋም ተገልጿል። በጉባኤው ላይ የሚሳተፉ እንግዶችን ለማስተናገድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለዕጩና ነባር ዲፕሎማቶች እንዲሁም ለበጎ ፍቃደኛ ወጣቶች ስልጠና በመስጠት ላይ ይገኛል። የስልጠናው ተሳታፊዎች በአዲስ አበባ እየተገነባ ያለውን የአዲስ ዓለም አቀፍ የኮንቬንሽንና ኤግዚቢሽን ማዕከል እንዲሁም የኮሪደር ልማት ስራዎችንና የተለያዩ የመሰረተ ልማት ዝርጋታዎችን ጎብኝተዋል። በጎ ፍቃደኛ ወጣት ምርትነሽ ካሳሁን ለኢዜአ በሰጠችው አስተያየት በ38ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባዔ ኢትዮጵያን የማስተዋወቅ እድል በማግኘቴ ደስተኛ ነኝ ብላለች። በኢትዮጵያ የተፈጠረው ሠላምና መረጋጋት እንዲሁም ቀጣይነት ያለው የኢኮኖሚ እድገት ለገጽታ ግንባታው ትልቅ ሚና እንዳለው ተናግራለች። በጎ ፍቃደኛ ወጣት ባቻክ ኡጁሉ በበኩሉ በጉብኝቱ የተመለከተው የልማት እና የመሰረተ ልማት ዝርጋታ የኢትዮጵያን ገጽታ ለመገንባት ተጨማሪ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ነው ያስታወቀው። ያገኘሁት ዕድል ለአገሬ የሚጠበቅብኝን አስተዋጽኦ ለማበርከት መልካም አጋጣሚ ፈጥሮልኛል ብሏል፡፡ ከስልጠናው ባገኘሁት ዕውቀት በመታገዝ የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ በሚጠበቀው ደረጃ ለማስተዋወቅ ቁርጠኛ ነኝ ሲልም አክሏል። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የኮንፍረንስ፣ ሁነትና የመንግሥት ፕሮቶኮል ዳይሬክተር እሸቱ ለገሰ በበኩላቸው፥ በአፍሪካ ህብረት ጉባዔ ላይ የሚሳተፉ እንግዶች ኢትዮጵያ የደረሰችበትን ደረጃ እንዲገነዘቡ የሚያስችል አስፈላጊው የቅድመ ዝግጅት ሥራ መከናወኑን አስታውቀዋል። በተለያዩ ቋንቋዎች የኢትዮጵያን ገጽታ የሚያስተዋውቁ በጎ ፍቃደኞች ስልጠና በመውሰድ ላይ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል፡፡ ዛሬ የተደረገው ጉብኝት ሰልጣኞች በቂ ግንዛቤ ጨብጠው አገራቸውን እንዲያስተዋውቁ ያለመ መሆኑን ነው የገለጹት። የውጭ ጉዳይ ኢኒስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር በረከት ድሪባ በ38ኛው የህብረቱ ጉባኤ የሚሳተፉ እንግዶች የኢትዮጵያን ገጽታ በላቀ ደረጃ እንዲረዱ በቂ ዝግጅት መደረጉን አስታውቀዋል። በጎ ፍቃደኞቹ የውጭ ጉዳይ ዲፕሎማሲን ጨምሮ እንግዶችን ተቀብሎ በማስተናገድ ረገድ ልምድ ባላቸው አሰልጣኞች ግንዛቤ እንዲጨብጡ በመደረግ ላይ መሆኑን ነው ያስታወቁት። ኢትዮጵያ ከኮንፍረንስ ቱሪዝም ይበልጥ እንድትጠቀም የሰለጠነ የሰው ኃይል ወሳኝ በመሆኑ መሰል ስልጠናዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።
በኬኒያ የተለያዩ አካባቢዎች እየጣለ ያለው ከባድ ዝናብ በርካቶችን ከቄያቸው አፈናቀለ
Dec 1, 2024 2454
አዲስ አበባ፤ህዳር 22/2017(ኢዜአ)፦በኬኒያ የተለያዩ አካባቢዎች እየጣለ ያለው ከባድ ዝናብ በርካቶችን ከቄያቸው ማፈናቀሉ ተገለጸ። የኬንያ መንግስት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የጣለውን ከባድ ዝናብ ተከትሎ ተጨማሪ የጎርፍ አደጋ ሊከሰት እንደሚችል ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል። በኬኒያ የተለያዩ አካባቢዎች ወቅቱን ያልጠበቀ ከባድ ዝናብ እየጣለ ነው። የአደጋ ምላሽ ቡድን አባላት በሚጥለው ከባድ ዝናብ ምክንያት በደረሰው የጎርፍ አደጋ የተጎዱ ከ240 በላይ አባወራዎችን አደጋ ከደረሰበት ሥፍራ ማንሳት መጀመራቸውን የሀገር ውስጥና ብሔራዊ አስተዳደር ሚኒስቴር በኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ በሰጠው መግለጫ ማስታወቁን ዥንዋ ዘግቧል። ሚኒስቴሩ በቪክቶሪያ ሀይቅ ተፋሰስ እና በሰሜን ምዕራብ ክልሎች ከፍተኛ ዝናብ በመጣሉ የጎርፍ አደጋ መከሰቱን በመግለጫው አስታውቋል። "የአደጋ ምላሽ ቡድኑ ከብሔራዊ የመንግስት አስተዳደር ጋር በመተባበር በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ያለውን ሁኔታ በመከታተል ለተጎዱ ወገኖች ድጋፍ እየሰጡ ነው" ሲል ዘገባው አመልክቷል። በሳምንቱ መጨረሻ እርጥበት አዘል አውሎ ነፋሶች ይጠበቃል ሲል ያመለከተው ዘገባው፤ የሰሜን እና ምስራቃዊ ኬንያ እንዲሁም የባህር ዳርቻ እና የስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች የጎርፍ ማስጠንቀቂያዎች መሰጠታቸውንም አክሏል። ይሁን እንጂ በሚቀጥለው ሳምንት ዝናቡ ሊቀንስ የሚችልባቸው ሁኔታዎች እንደሚኖሩ የሚኒስቴሩን መግለጫ ጠቅሶ ዥንዋ አስታውቋል። ሚኒስቴሩ በተጨማሪም ሀይቅ ዳር በሆነችው ኪሱሙ 200 የሚጠጉ አባዎራዎች መጎዳታቸውን አመልክቶ፤ 100 ሄክታር ማሳ ላይ የተዘሩ ሰብሎች መውደማቸውን ጠቁሟል። "ለደህንነታቸው ሲባል ለጊዜው ወደ ሌላ ቦታ የሚዘዋወሩ የጎርፍ ተጋላጭ አካባቢ ነዋሪዎች የአደጋ ምላሽ ከሚሰጡ ቡድኖች ጋር እንዲተባበሩ ሚኒስቴሩ ማሳሰቡን" ዘገባው አመክቷል። 2024 መጀመሪያ ላይ የጣለው ያልተለመደ ዝናብ ኤልኒኖ ተብሎ ከሚጠራው የአየር ሁኔታ ጋር ተዳምሮ ለአየር ንብረት ለውጥ በጣም ተጋላጭ በሆነችው በኬንያ ከፍተኛ ጉዳት ማስከተሉን ዘገባው አስታውሷል። በኬኒያ በመጋቢት እና ሰኔ መካከል በጣለው ከባድ ዝናብ እና ጎርፍ ከ300 በላይ ሰዎችን ህይወት መቅጠፉን ያመለከተው ዘገባው፣ በዚህ ወቅት 188 ሰዎች ቆስለዋል፣ 38 የሚሆኑት ሌሎች ሰዎች ደግሞ ደብዛቸው መጥፈቱን ዘገባው ጠቁሟል። በነዚሁ ጊዚያት በጎርፉ ምክንያት ከ293 ሺህ 200 በላይ ሰዎች ተፈናቅለው ወደ 306 ሺህ 520 የሚጠጉ ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው ከብሔራዊ የአደጋ መከላከል ማእከል ያገኘውን መረጃ ጠቅሶ ዥንዋ ዘግቧል።
እየተባባሰ የመጣው የሶማሊያ ፖለቲካዊ ቀውስ
Nov 27, 2024 2194
አዲስ አበባ፤ ህዳር 18/2017(ኢዜአ)፦ በሶማሊያ ፓርላማ ዛሬ ከፍተኛ ብጥብጥ ተከስቷል። የሶማሊያ መንግስት አካሄድን የተቃወሙ የሀገሪቱ የፓርላማ አባላት ቁጣቸውን በፓርላማ ውስጥ ሲገልጹ ታይተዋል። የሶማሊያ ፓርላማ ባወጣው መግለጫ የሀገሪቱ መንግሥት የሶማሊያ ጦር አልሸባብን ከመዋጋት ይልቅ በጎሳ ክፍፍል እንዲወጠር በማድረግ የያዛቸውን ቦታዎች እንኳ እንዳያስተዳድር አድርጓል ብሏል። በሀገሪቱ ሙስና ስር እየሰደደ ከመምጣቱም ባሻገር መንግስት ጦሩን ለፖለቲካ ፍጆታ እየተጠቀመ መሆኑንም ነው ፓርላማው በመግለጫው ያስታወቀው። ይህም በሀገሪቱ የጎሳ ክፍፍል እንዲፈጠር እያደረገ መሆኑንም አስታውቋል። ከሶማሊያ ህገ መንግስት ባፈነገጠ መልኩ የሀገሪቱ መንግስት የክልላዊ አስተዳደሮችን መብቶች እየተጋፋ መሆኑንም እንዲሁ። የሶማሊያ መንግስት ሶማሊያውያንን በጎሳ ለመከፋፈል የሚያደርገው ሙከራ በአስቸኳይ እንዲቆምም ጠይቀዋል። የሀገሪቱ መንግስት ከመሰል አደገኛ አካሄዱ ካላቆመም ሶማሊያ የመፍረስ አደጋ እንደሚገጥማት የፓርላማ አባላቱ ባወጡት መግለጫ አስጠንቅቀዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም