ዓለም አቀፍ ዜናዎች
ኢትዮጵያን ጨምሮ በአፍሪካ በ2024 በርካታ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ያሏቸው 10 አገራት ይፋ ሆኑ 
Jul 22, 2024 645
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 15/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያን ጨምሮ በአፍሪካ በ2024 በርካታ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ያሏቸው 10 አገራት ይፋ ተደረጉ። የሩሰያ ዜና አገልግሎት ስፑትኒክ እንደዘገበው ናይጄሪያ ከሁሉም አገራት የቀዳሚነቱን ስፍራ ይዛለች። ኢትዮጵያ ደግሞ ከኬኒያና ታንዛኒያን ቀድማ በስምንተኛ ደረጃ ላይ ስትገኝ ታንዛኒያ በመጨረሻው በ10ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ዘገባው ያሳያል። የደረጃ አሰጣጡ መሰረት ያደረገው ከ80 ሺህ በላይ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ተመርኩዞ መሆኑን ስፑትኒክ ጠቁሞ መስፈርቱ ከ22 ሺህ 500 በላይ የመረጃ ምንጮችን የሸፈነ እንደሆነም አመልክቷል። ለደረጃ አሰጣጡ ኦንላይን ስታትስቲክስ ፖርታል በመጠቀም መረጃዎችን የመሰብሰብ ስራ መከናወኑ ተገልጿል። በአፍሪካ አገራት በይነ መረብ ወይም ኢንተርኔት በተመጣጣኝ ዋጋ ባላቸው መሳሪያዎች ተደራሽነት በአሁኑ ወቅት እያደገ መምጣቱን በዘገባው ተገልጿል። በተጨማሪም የተሻለ የቴሌኮም ግንኙነት በተለይም የዲጂታል አገልግሎቶች በመስፋፋታቸው ምክንያት የዓለም አቀፍ እና የአፍሪካ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ቁጥር በአሁኑ ወቅት ማሻቀቡን ቀጥሏል ብሏል ስፑትኒክ በዘገባው። በአፍሪካ ያለው የኢንተርኔት አጠቃቀም ምንም እንኳን ከሌሎች ክፍለ ዓለማት ጋር ሲነጻጸር አሁንም በዝቅተኛ ደረጃ ላይ ቢሆንም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን አስደናቂ እድገት መታየቱን ዘገባው አስታውሷል። ዘገባው እ.ኤ.አ. በ2024 የኢንተርኔት አጠቃቀምን የሚመሩ አስር የአፍሪካ ሀገራትን ዝርዝር እንሚመለከተው አስቀምጧል፡- 1. ናይጄሪያ (103 ሚሊዮን ወይም 45 ነጥብ 2 በመቶ የህዝብ ብዛት)፣ 2. ግብፅ (82 ሚሊዮን ወይም 76 በመቶው ህዝብ)፣ 3. ደቡብ አፍሪካ (45 ሚሊዮን ወይም ከህዝቡ 72 ነጥብ በመቶ)፣ 4. ሞሮኮ (34 ሚሊዮን ወይም 92 ነጥብ 2 በመቶው የህዝብ ብዛት)፣ 5. አልጄሪያ (33 ሚሊዮን ወይም 71 ነጥብ 8 በመቶ የህዝብ ብዛት)፣ 6. ዲሞክራቲክ ኮንጎ (28 ሚሊዮን ወይም 27 ነጥብ 4 በመቶ የህዝብ ብዛት)፣ 7. ጋና (24 ሚሊዮን ወይም 71 ነጥብ 3 በመቶ የህዝብ ብዛት)፣ 8. ኢትዮጵያ (24 ሚሊዮን ወይም 21 ነጥጭብ 1 በመቶ የህዝብ ብዛት)፣ 9. ኬንያ (22 ሚሊዮን ወይም 43 ነጥብ 3 በመቶው የህዝብ ብዛት)፣ 10. ታንዛኒያ (21 ሚሊዮን ወይም ከህዝቡ 33 ነጥብ 4 በመቶ
በአፍሪካ ቀንድ በመጪዎቹ ሶስት ወራት ከወትሮው የተለየ የሙቀት መጠን ሊኖር ይችላል  
Jul 21, 2024 549
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2016(ኢዜአ)፦ በአፍሪካ ቀንድ በመጪዎቹ ሶስት ወራት ከወትሮው የተለየ የሙቀት መጠን ሊኖር ይችላል። የኢጋድን በይነ መረብ ዋቢ አድርጎ ዥንዋ እንደዘገበው፤ በአፍሪካ ቀንድ ከነሐሴ እስከ ጥቅምት ወራት ባለሉት ጊዜያት ከወትሮው የበለጠ የሙቀት መጠን ይኖረዋል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) የአየር ንብረት ትንበያ ኤጀንሲ የአፍሪካ ቀንድ ቀጠና ከነሀሴ እስከ ጥቅምት ባሉት ወራት ከወትሮው የበለጠ ሙቀት እንደሚኖረው ትናንት ማስታወቁን ዘገበው አመልክቷል። የኢጋድ የአየር ንብረት ትንበያ ማመልከቻ ማእከል ያስታወቀው፤ በአካባቢው በሚገኙ አንዳንድ ሀገራት የሙቀቱ መጠን እስከ 35 ዲግሪ ሴልሺየስ ሊደርስ እንደሚችልም ነው የጠቆመው። ይሁን እንጂ ከሙቀቱ በተጋዳኝ በአንዳንድ አካባቢዎች ከወትሮው የተለየ ቀዝቃዛ የአየር ንብረት ሊስተዋል እንደሚችል ድርጅቱ አስታውቋል። ሌሎች እንደ ጂቡቲ ፡ ኬንያ ፡ ደቡብ ሱዳን ፡ ሱማሊያና ኡጋንዳ በመሳሰሉት የአፍሪካ ቀንድ ሀገራት ከፍተኛ የሙቀት መጠን የሚመዘገቡባቸው እንደሆኑም ዥንዋ በዘገባው አመላክቷል። በአካባቢው ከሚከሰተው ከፍተኛ ሙቀት በተጨማሪም ከነሀሴ እስከ ጥቅምት ባሉት ወራት የአፍሪካ ቀንድ ምስራቃዊ ክፍሎች ከወትሮው የበለጠ ደረቅ የአየር ንብረት እንደሚያጋጥማቸው የማዕከሉ ትንበያ ያመለክታል።
የተዛባ የእንቅልፍ ሰዓት ለስኳር በሽታ እንደሚያጋልጥ ተመላከተ
Jul 19, 2024 655
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 11/2016(ኢዜአ)፡- መደበኛ ያልሆነ ወይም የተዛባ የእንቅልፍ ሰዓት በስኳር በሽታ የመያዝ እድልን እንደሚጨምር ተመላክቷል። የዩናይትድ ኪንግደም ባዮባንክ ያካሄደው ተከታታይ ጥናት መደበኛ ያልሆነ የመኝታ ሰዓት አጠቃቀም ለታይፕ 2 ስኳር በሽታ አጋላጭ ምክንያቶች ሰፊ ድርሻ እንደሚኖረው አስገንዝቧል። የተለያየ የመኝታ ሰዓት የሚጠቀሙና መደበኛ የእንቅልፍ ቆይታ የሌላቸው ሰዎች ለስኳር በሽታ ተጋላጭ እንደሚሆኑ ነው ጥናቱ ያመለከተው። ጥናቱ የተካሄደው በአማካይ 62 አመት የሞላቸው 84 ሺህ ስኳር ታማሚ ባልሆኑ ግለሰቦች ላይ ሲሆን ለ7 ተከታታይ ቀናት የእንቅልፍ ሰዓታቸው ላይ ቁጥጥር ሲደረግ ነበር። በጥናቱ ውጤት መሰረት "መደበኛ ያልሆነ" የእንቅልፍ ሰዓት ተብሎ የተለየው በየቀኑ በአማካይ ከ1ሰዓት በላይ የሚለዋወጥ የእንቅልፍ ቆይታ መሆኑን ዩፒአይ ዘግቧል። በዚህም ከ60 ደቂቃ በላይ በየቀኑ የእንቅልፍ ሰዓታቸው የሚዛባ 34 በመቶው የጥናቱ ተሳታፊዎች ለስኳር ተጋላጭ መሆናቸውን ጥናቱ እንዳመለከተ ተገልጿል። በተጨማሪም የጥናቱ ተሳታፊዎች ባለፉት ሰባት ዓመታት ባጋጠማቸው የስኳር በሽታ ተጋላጭነት ላይ የዳሰሳ ጥናት መደረጉም ተመልክቷል። የጥናት ቡድኑ ለስኳር በሽታ ተጨማሪ አጋላጭ የሆኑ ምክንያቶችን ከለየ በኋላ የተዛባ ወይም መደበኛ ያልሆነ የእንቅልፍ ሰዓት ለታይፕ 2 ሰኳር በሽታ አጋላጭ ምክንያት መሆኑን አረጋግጧል። የጥናት ቡድኑ መሪ የሆኑት ሲና ኪያነርሲ ወጥነት ያለው የእንቅልፍ ሰዓት በታይፕ 2 ስኳር በሽታ የመያዝን እድል ለመቀነስ ጉልህ ድርሻ እንዳለው በጥናቱ መረጋገጡን ተናግረዋል።
በኮትዲቯር በደረሰ የመሬት መንሸራተትና የጎርፍ አደጋ የ24 ሰዎች ህይወት አለፈ
Jun 26, 2024 2347
  አዲስ አበባ፤ ሰኔ 18/2016 (ኢዜአ)፦በኮትዲቯር ትልቋ የኢኮኖሚ ከተማ አቢጃን በተከሰተ የመሬት መንሸራተትና የጎርፍ አደጋ የ24 ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተነገረ። በምዕራብ አፍሪካ ሃገራት ከመደበኛው ከፍ ባለ መልኩ እየጣለ ያለውን ከባድ ዝናብ ተከትሎ በኢኮኖሚ ከተማዋ አቢጃን ባለፉት 10 ቀናት በተከታታይ የጣለው ዝናብ የተፈጥሮ አደጋዎችን አስከትሏል። በዚህም በመላው ሃገሪቱ ያሉ የውሃ አካላት ከፍታ የጨመረ ሲሆን የጎርፍ መጥለቅለቅና የመሬት መንሸራተትም ተከስቷል። ዝናቡ ባስከተለው ጎርፍና የመሬት መንሸራተት አደጋም 24 ሰዎች ሕይወታቸው ማለፉን የሀገሪቱ ባለስልጣናት አስታውቀዋል። ከአደጋው ጋር በተያይዘ ሁለት ሰዎች የደረሱበት አለመታወቁን ያመለከተው የሲጂቲኤን ዘገባ በክስተቱ የህንጻዎች መደርመስ አደጋ ሊያጋጥም እንደሚችል ማስጠንቀቂያ መሰጠቱን አስነብቧል። ለሚቀጥሉት ሶስት ወራት በሚቆየው የሀገሪቱ የክረምት ወቅት አስቸጋሪ የተፈጥሮ ክስተት ሊያጋጥም እንደሚቸልም በዘገባው ተመልክቷል። All reactions: 127127
17ተኛውን የአውሮፓ ዋንጫ የሚያስተናግዱትን 10 ስታዲየሞች እንተዋወቃቸው
Jun 14, 2024 2228
የብዙዎችን ቀልብ በመሳብ የሚታወቀው የአውሮፓ ዋንጫ ውድድር እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ1960 በፈረንሳይ አስተናጋጅነት መጀመሩ ይታወቃል፡፡ በመጀመሪያው የአውሮፓ ዋንጫ ሶቪየት ዩኒየን ዩጎዝላቪያን 2 ለ 1 በመርታት አሸናፊ የሆነችበት ውድድር ዘንድሮ ለ17ተኛ ጊዜ በጀርመን አስተናጋጅነት ከሰኔ 7 እስከ ሐምሌ 7 ቀን 2016 ዓ.ም ይከናወናል። በውድድሩ 24 አገራት በስድስት ምድብ ተከፍለው ጨዋታቸውን የሚያከናውኑ ሲሆን እነዚህ ውድድሮች በጀርመን 10 ከተሞች በሚገኙ አሥር ስታዲየሞች ይከናወናሉ። 17 ተኛውን የአውሮፓ ዋንጫ የሚያስተናግዱትን 10 ስታዲየሞችን እንተዋወቃቸው፡- የበርሊን ኦሊምፒክ ስታዲየም በጀርመን ዋና ከተማ በርሊን የሚገኝ ሲሆን 71ሺህ ተመልካች ይይዛል። የጀርመኑ ሀርታበርሊን ክለብ የሚጫወትበት ይኼ ስታዲየም 6 ጨዋታዎች የሚደረጉበት ሲሆን ስፔን ከክሮሽያ፣ ፖላንድ ከኦስትሪያ እና ኔዘርላንድ ከኦስትርያ የሚያደርጉትን የምድብ ጨዋታ፤ እንዲሁም ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል። በተጨማሪም የሩብ ፍፃሜ እና የፍፃሜ ጨዋታዎች ይደረጉበታል። ሬንኢነርጂ ስታዲየም ይህ ስታዲየም በጀርመኗ ኮሎኝ ከተማ ይገኛል። 43 ሺህ ተመልካች የሚይዝ ሲሆን የጀርመኑ ክለብ ኮሎኝ የሚጠቀምበት ስታዲየም ነው። በአውሮፓ ዋንጫው 5 ጨዋታዎቸን ያስተናግዳል። ሀንጋሪ ከሲውዘርላንድ፤ ስኮትላንድ ከሲውዘርላንድ፤ ቤልጂየም ከሮማንያ፤ ኢንግላንድ ከስሎቬኒያ እና እንዲሁም ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል። አሊያንዝ አሬና ይህ ስታዲየም የጀርመኑ ክለብ ባየርሙኒክ የሚጫወትበት ስታዲየም ሲሆን፤ከ75 ሺህ ተመልካች በላይ ይይዛል። 6 ጨዋታዎች የሚደረጉበት ሲሆን ጀርመን ከስኮትላንድ፤ ሮማንያ ከዩክሬን፣ ስሎቬኒያ ከሰርቢያ፤ ዴንማርክ ከሰርቢያ፤ እንዲሁም ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል። በተጨማሪም አንድ የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታ ያስተናግዳል። ፍራንክፈርት አሬና በጀርመኗ ከተማ ፍራንክፈርት የሚገኝ ሲሆን፤47 ሺህ ተመልካቾችን ይይዛል። የጀርመኑ ክለብ ኢንትራ ፍራንክፈርት የሚጠቀምበት ስታዲየም ሲሆን 5 ጨዋታዎችን ያስተናግዳል። ቤልጂየም ከስሎቬክያ፤ዴንማርክ ከኢንግላንድ፣ ስዊዘርላንድ ከጀርመን፤ስሎቫኪያ ከሮማንያ የሚያደርጉትን የምድብ ጨዋታና እና እንዲሁም ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል። ቮልክ ስፓርክ ይህ ስታዲየም በጀርመኗ ሀምቡሩግ ከተማ የሚገኝ ሲሆን 49 ሺህ ተመልካቾችን ይይዛል። የጀርመኑ ክለብ ሀምቡርግ የሚገለገልበት ሲሆን በአውሮፓ ዋንጫ 5 ጨዋታዎችን ያስተናግዳል።ፖላንድ ከኔዘርላንድ ፤ክሮሽያ ከአልቤኒያ ፤ ጆርጂያ ከቼክሪፐብሊክ ፤ቼክ ሪፐብሊክ ከተርኪዬ የሚያደርጉትን የምድብ ጨዋታና ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል። ሲግናል አዱና ፓርክ ይህ ስታዲየም በጀርመኗ ዶርትሙንድ ከተማ የሚገኝ ሲሆን ከ81ሺህ በላይ ተመልካች ይይዛል። በቦሪሲያ ዶርትሙነድ ክለብ ባለቤትነት የተያዘው ስታዲየሙ 6 ጨዋታዎችን የሚያስተናግድ ሲሆን ጣሊያን ከአልቤኒያ፤ ተርኪዬ ከጆርጂያ፤ተርኪዬ ከፖርቹጋል ፣ ፈረንሳይ ከፖላንድ ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል። በተጨማሪም አንድ የግማሽ ፍፃሜም ጨዋታም ያስተናግዳል። ላይፕዚግ ስታዲየም ይኼ ስታዲየም የጀርመኑ ክለብ አርቢ ላይፕዚግ የሚጫወትበት ሲሆን 40ሺህ ተመልካች ይይዛል ።በአውሮፓ ዋንጫው 4 ጨማታዎችን ያስተናግዳል። ፖርቹጋል ከቼክ ሪፐብሊክ ፤ ኔዘርላንድ ከፈረንሳይ ፤ክሮሽያ ከጣሊያን የሚያደርጉትን ምድብ ጨዋታ ጨምሮ ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል። አሬና አፍሻልክ ስታዲየም ይህ ስታዲም በጀርመኗ ከተማ ግላሰንከርከን ከተማ ይገኛል። የጀርመኑ ክለብ ሻልክ 04 የሚጠቀምበት ይህ ስታዲየም 50 ሺህ ተመልካቾችን የመያዝ አቅም ያለው ሲሆን በውድድሩ 4 ጨዋታዎችን ያስተናግዳል። ሰርቢያ ከእንግሊዝ፤ ስፔን ከጣሊያን፤ጆርጂያ ከፖርቹጋልና እንዲሁም ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል። ስቱትጋርት አሬና ይህ ስታዲም በጀርመኗ ከተማ ስቱትጋርት የሚገኝና የጀርመኑ ክለብ ስቱትጋርት የሚጠቀምበት ስታዲየም ነው። ስሎቬኒያ ከዴንማርክ፤ጀርመን ከሀንጋሬ፤ስኮትላንድ ከሀንጋሬ፤ዩክሬን ከቤልጂየም የሚያደርጉትን የምድበ ጨዋታዎች ፣በተጨማሪም አንድ የሩብ ፍፃሜ ጨዋታን ያስተናግዳል። ዱሴልዶርፍ አሬና በጀርመኗ ከተማ ዱሴልዶርፍ የሚገኝ ሲሆን 47 ሺህ ተመልካች የመያዝ አቅም አለው።ስታዲየሙ 5 ጨዋታዎችን የሚያስተናግድ ሲሆን ኦስትርያ ከፈረንሳይ፤ስሎቬኪያ ከዩክሬን፤አልቤኒያ ከስፔን የሚያደርጉትን የምድብ ጨዋታና እንዲሁም ከ16 ቱ የጥሎ ማለፍ ጨዋታዎች አንዱን ያስተናግዳል።። በተጨማሪም አንድ የሩብ ፍፃሜ ጨዋታ ይደረግበታል።        
ሰው ሰራሽ አስተውሎት የመረጃ ስርጭትን በፍጥነት እየተለወጠ ባለበት አለም አፍሪካ ትክክለኛ ድምጿን እንድታሰማ ሀገራት ለዘርፉ ትኩረት እንዲሰጡ ጥሪ ቀረበ
May 16, 2024 2453
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 8/2016(ኢዜአ)፦ ከሰው ሰራሽ አስተውሎት ጋር በተገናኘ የመረጃ ስርጭት በፍጥነት እየተለወጠ ባለበት አለም አፍሪካ ትክክለኛ ድምጿን እንድታሰማ ለማድረግ ሀገራት ለዘርፉ ተገቢውን ትኩረት እንዲሰጡ ጥሪ ቀረበ። በአህጉሪቱ የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፍ ላይ የሚመክረው 3ተኛው የአፍሪካ ሚዲያ ኮንቬንሽን በጋና አክራ እየተካሄደ ይገኛል። አፍሪካዊ መረጃዎችን ለአርቴፍሻል አስተውሎት ግብአት በሚሆን መልኩ በማዘጋጀትና የአህጉሪቱን መጪ የቴክኖሎጂ ጉዞ በማፋጠን በኩል ሚዲያው ከፍተኛ ሚና እንዳለው በጉባኤው ተነስቷል። የዘንድሮው ጉባኤ የሚዲያ ነፃነትና የመረጃ ተደራሽነት እንዲሁም ሚዲያውን በኢኖቬሽንና በሰው ሰራሽ አስተውሎት የማገዝ አጀንዳዎችን መያዙ ተገልጿል። በተጨማሪም የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ሀገራት የሚወስዱትን መፍትሄዎች ለብዙሃኑ መረጃ የማድረስ ሃላፊነታቸውን ሚዲያዎች እንዲወጡ ማድረግ ላይም ጉባኤው ይመክራል ተብሏል።   በ3ተኛው የአፍሪካ ሚዲያ ኮንቬንሽን ላይ የሀገራት የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ የአፍሪካ ህብረትና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስራ መሪዎችና ከመላው አፍሪካ የተውጣጡ የሚዲያ ባለሙያዎች ተሳታፊ ናቸው። ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ጉባኤ ኢትዮጵያ በተለይ በሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ በሚዲያና ኮሙኒኬሽን ዘርፎች የምታከናውናቸውን ተግባራት በተመለከተ ልምዷን እንደምታካፍል የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት መረጃ ያመላክታል።
በእስራኤልና ኢራን መካከል የሚታየውን አሳሳቢ ሁኔታ ሀገራት በአስቸኳይ ሊያስቆሙት ይገባል- አንቶኒዮ ጉተሬዝ
Apr 15, 2024 2664
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7/2016(ኢዜአ)፡- አለም ተጨማሪ ጦርነት እንድታስተናግድ እድል ባለመፍጠር በእስራኤልና ኢራን መካከል የሚታየውን አሳሳቢ ሁኔታ ሀገራት በአስቸኳይ ሊያስቆሙት እንደሚገባ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ አሳሰቡ። ኢራን እስራኤል ከሳምንታት በፊት ሶርያ በሚገኘው ቆንስላ ጽሕፈት ቤት ጥቃት አድርሳብኛለች በሚል ባሳላፍነው ቅዳሜ ሌሊት መጠነ ሰፊ ጥቃት መሰንዘሯ በተለያዩ የዓለም መገናኛ ብዙሃን መዘገቡ ይታወሳል። ይህንንም ተከትሎ በቀጣናውና በአለም ሀገራት የተፈጠረውን ከፍተኛ ውጥረት ለማርገብ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ የጸጥታ ምክር ቤቱን አስቸኳይ ስብሰባ ጠርተዋል። በስብሰባውም አለም ተጨማሪ ጦርነት የምታስተናግድበት ምንም አይነት አቅም ስለሌለ ሀገራት በእስራኤልና ኢራን መካከል የሚታየውን አሳሳቢ ሁኔታ በአስቸኳይ ሊያስቆሙት ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። ችግሩ በቸልታ የሚታይ ከሆነ አስከፊ ጉዳት ሊያስከትል እንደሚችል መናገራቸውን ያስነበበው ፍራንስ 24 የጸጥታው ምክር ቤት አባላት ሁኔታውን በአስቸኳይና ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ሊያስቆሙት እንደሚገባ ማሳሰባቸውንም ዘግቧል።
በሞዛምቢክ በደረሰ የጀልባ አደጋ ህጻናትን ጨምሮ ከ90 በላይ ሰዎች ሕይወት አለፈ
Apr 8, 2024 3100
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 30/2016(ኢዜአ)፦በሞዛምቢክ ሰሜናዊ ክፍል የባህር ዳርቻ በተከሰተ የጀልባ አደጋ ህጻናትን ጨምሮ ከ90 በላይ ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተገለጸ። በሞዛምቢክ ሰሜናዊ ክፍል በምትገኘው ናምፑላ ግዛት 130 የሚሆኑ ሰዎችን አሳፍራ ስትጓዝ የነበረች ጀልባ መስጠሟን የሀገሪቱ ባለስልጣናት አስታውቀዋል። ነዋሪዎቹ በግዛቷ የተከሰተውን የኮሌራ ወረርሽኝ በመሸሽ ወደ ሌላ አካበቢ ለመሄድ በጀልባ በተሳፈሩበት ወቅት አደጋው እንደተከሰተ የገለጹት ባለስልጣናቱ ጀልባዋ መሸከም ከምትችለው የሰው መጠን በላይ በመጫኗ አደጋው እንደደረሰ አመልክተዋል። በዚህም ህጻናትን ጨምሮ ከ90 በላይ ሰዎች ሕይታቸው እንዳለፈ ማረጋገጣቸውን ቢቢሲ ዘግቧል። በአሁኑ ወቅት አምስት ሰዎችን ከአደጋው በሕይወት ማትረፍ እንደተቻለ ያመለከተው ዘገባው ተጨማሪ ሰዎችን ለማዳን ርብርብ እየተደረገ መሆኑን አስነብቧል። የናምፑላ ግዛት ባለፈው አመት በሞዛምቢክ በተከሰተው የኮሌራ ወረርሽኝ ክፉኛ ከተጎዱ አካባቢዎች መካከል አንዷ መሆኗም በዘገባው ተመላክቷል።
የአየር ንብረት ለውጥና መዘዙ
Apr 5, 2024 1969
በዓለማችን ላይ እየተስተዋለ ያለው የአየር ንብረት ለውጥ የተወሳሰበ ችግር እያስከተለ ከመሆኑ በተጨማሪ በስነምህዳር ላይ እያደረሰ ያለው አደጋ ሊቀለበስ ወደ ማይችልበት ደረጃ ላይ እየደረሰ መሆኑን ሞደርን ዲፕሎማሲ ድረገጽ አስነበበ። ድረ ገጹ በዓለማችን በየዓመቱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎች የአየር ንብረት ለውጥ በሚያስከትለው ድርቅ፣ ጎርፍ እና ተዛማጅ በሆኑ ክስተቶች ምክንያት ቀያቸውን ጥለው ለመሰደድ እንደሚገደዱ አስነብቧል። የአየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ በይነመንግስታት ያወጣው መረጃ እንደሚያመለክተው አሁን ላይ ያለው የዓለማችን የሙቀት መጠን ወደ 1 ነጥብ 5 ዲግሪ ሴሊሺየስ እየተጠጋ በመምጣቱ በስነምህዳር፣ በከባቢ አየር እና በአካባቢ ላይ ከፍተኛ ለውጥ እየተስተዋለ መሆኑን ገልጿል። የአየር ንብረት ለውጥ ለዘላቂ ልማት እንቅፋት በመሆን ተፈጥሮአዊና ሰው ሰራሽ ክስተቶች የሚፈጥራቸውን ችግሮች በማባባስ ለሰዎች መፈናቀልና የህይወት መጎሳቆል እያደረሰ ይገኛል። እንደአውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ2020 በማዕከላዊ አሜሪካ እና ደቡባዊ ሜክሲኮ የተከሰተው ሃሪኬን ኤታ የተባለው የአየር ንብረት ለውጥ ክስተት ያስከተለው የሰብል ውድመትና የመሰረተ ልማት አውታሮች ላይ የደረሰው አደጋ ከባለፉት ሁለት አስርተ ዓመታት ውስጥ እጅግ የከፋ አደጋ መሆኑን ዘገባው አመልክቷል። በዚህም በጎርፍ፣ በመሬት መንሸራተትና በሰብል ውድመት ምክንያት ከ1 መቶ 20 ሺህ በላይ ሰዎችን ከሞቀ መኖሪያቸው ተፈናቅለው እርዳታ ጠባቂ እንዳደረጋቸው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከፍተኛ የስደተኞች ኮሚሽንን መረጃ ዋቢ አድርጎ አትቷል። የአየር ንብረት ለውጥ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ መምጣቱን የጠቆመው ድረ ገጹ በቀጣይ ተመሳሳይ ችግሮች ሊያጋጥሙ እንደሚችሉም አመልክቷል። በአውሮፓውያኑ 2022 ወደ 32 ሚሊየን የሚጠጉ ሰዎች በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የተፈናቀሉ ሲሆን፤ ይህ አሃዝ በ2008 ከተከሰተው በ41 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱን ዘገባው አመልክቷል። ይህም የዓለማችን የሙቀት መጠን እየጨመረ መምጣቱን እንጂ ምንም ዓይነት የመቀነስ አዝማሚያ ያላሳየ መሆኑን ያመለከተው ዘገባው በቺሊ፣ ካናዳ፣ ዛምቢያ፣ ሞዛምቢክ፣ ሜክሲኮ፣ ኢክዋዶር፣ ሊቢያ እና በሌሎችም አገራት ሃሪኬን በተሰኘው የአየር ለውጥ፣ በሰደድ እሳት፣ በጎርፍ እና በድርቅ ምክንያት ለባለፉት በርካታ ወራት መፈናቀልን እንዳስከተለ ተገልጻል። የአለም ባንክን የትንበያ መረጃ ዋቢ ያደረገው ድረ ገጹ በአውሮፓውያኑ 2050 ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር በተያያዘ 216 ሚሊዮን ሰዎች ሊፈናቀሉ እንደሚችሉ ተመላክቷል። ድረገጹ ይሄ ክስተት የሚያስከትላቸው ችግሮች እንዳይቀጥሉ መቆጣጠር ካስፈለገ ዘላቂ ልማት ላይ ያተኮሩ ግንዛቤን የሚያሳድጉ ትምህርቶች፣ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ እውነተኛ ውይይቶች እና ተፈጥሮን መሰረት ያደረጉ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎች ትኩረት ሊሰጣቸው እንደሚገባ በማሳሰብ መሪዎች የሚጠበቅባቸውን ሊተገብሩ ይገባል ሲል ምክሩን አስቀምጧል።  
በአባቱ የሎተሪ ስጦታ 4 ሚሊዮን ዶላር ያሸነፈው እድለኛ 
Apr 4, 2024 1674
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 26/2016(ኢዜአ)፦ በአሜሪካ ኤሊኖይ ግዛት ነዋሪ የሆነው ግለሰብ አባቱ ያበረከቱለት የሎተሪ ትኬት የ4 ሚሊዮን ዶላር እድለኛ አድርጎታል። ስቴቨን ሪቻርድስ ይባላል በኤሊኖይ የባሪንግተን ከተማ ነዋሪ ሲሆን ከቀናት በፊት ከአባቱ ጋር ቁርስ ለመመገብ ባቀኑበት ምግብ ቤት ከአባቱ ስጦታ ይበረከትለታል። ስጦታውም የ10 ዶላር የሎተሪ ትኬት ነበር። አዛውንቱ ያበረከቱለት የሎተሪ ትኬት ወዲያውኑ ተፍቆ ውጤቱን የሚያሳይ ሲሆን ስቴቨንም ትኬቱን በፋቀበት ቅጽበት ከፍተኛ ድንጋጤ እንደተሰማው ለማሳቹሴት የሎተሪ አስተዳደር ተናግሯል። የሎተሪ ትኬቱ የ4 ሚሊዮን ዶላር እድለኛ እንዳደረገኝ ሳውቅ በድንጋጤ ማመን አልቻልኩም በዚህም ውጤቱን ከመናገሬ በፊት በስልኬ ስካን አደረኩት ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል። በመቀጠለም የአባቱ ስጦታ እድለኛ እንዳደረገው ለባለቤቱ እንዲሁም ለአባቱ መናገሩን ዩፒአይ ዘግቧል። ስቴቨን በሎተሪ ከደረሰው 4 ሚሊዮን ዶላር ውስጥ በተወሰነው ገንዘብ ከባለቤቱ ጋር የተለያዩ አካባቢዎችን ለመጎብኘት ማቀዱን ዘገባው አመልክቷል።
የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት በሱዳን ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ ጥረቱን እንደሚቀጥል አስታወቀ
Apr 3, 2024 980
አዲስ አበባ ፤ መጋቢት 25/2016(ኢዜአ)፡- የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት በሱዳን ያለው ግጭት በዘላቂነት እንዲቆምና ሰላም እንዲመጣ ጥረቱን እንደሚቀጥል አስታወቀ። ምክር ቤቱ የተመሰረተበትን 20ኛ ዓመት በዓል እና ለአዲስ አባል ሀገራት የአቀባበል መርሃ ግብር አካሂዷል። አቀባበል የተደረገላቸው አንጎላ፣ ቦትስዋና፣ ኮትዲቯር፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ግብጽ፣ ኢኳቶሪያል ጊኒ፣ ጋምቢያ፣ ሴራሊዮን፣ ታንዛኒያ እና ኡጋንዳ ናቸው። የአፍሪካ ሕብረት የፖለቲካ ጉዳዮች፣ የሰላምና ጸጥታ ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር ባንኮሌ አዲኦዬ በዚህ ወቅት እንዳሉት፥ ምክር ቤቱ በአህጉሪቱ ሰላምና ጸጥታን ለማስፈን ባደረገው ጥረት ለውጥ መምጣቱን ተናግረዋል። የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነትን ለማቆምና ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ የተደረገው የሰላም ስምምነት የምክር ቤቱ የአፍሪካን ችግር በአፍሪካዊ ማዕቀፍ የመፍታት ሂደት ዐቢይ ማሳያ ነው ብለዋል። በምስራቅ አፍሪካ ቀጣና ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲኖር የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጸዋል። ምክር ቤቱ በሱዳን የተከሰተውን ግጭት በማቆም ዘላቂ ሰላም ለማምጣት ጥረት እያደረገ መሆኑንም አንስተዋል። ለዚህም ከአፍርካ ህብረት፣ ከኢጋድና ከጎረቤት ሀገራት ጋር በመሆን ተፋላሚ ሃይላትን የማነጋገርና ወደ ሰላማዊ ውይይት እንዲመጡ እየተሰራ ስለመሆኑ ጠቅሰዋል። በቅርቡ በሚካሄደው የምክር ቤቱ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ስብሰባ የሱዳን ጉዳይ በልዩ ትኩረት ምክክር እንደሚደረግበት ኮሚሽነሩ ጠቁመዋል። በአፍሪካ ግጭቶችን የመፍታትና እንዳይከሰቱ የመከላከል ጥረቶች ውጤታማ እንዲሆኑ የአፍሪካ ህብረት ለሰላምና ጸጥታ ምክር ቤቱ ድጋፍ ማድረጉን እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት በቀይ ባህር አካባቢ የሚስተዋሉ ግጭቶች በምስራቅና ሰሜን የሚገኙ አባል አገራት ላይ የሚያመጣውን ተጽእኖ በመረዳት ከሚመለከታቸው ጋር እንደሚሰራ ጠቁመዋል። ግጭትን አስቀድሞ መከላከል፣ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት የሚያስችል አቅምና ትብበር ማጠናከር፣ የዴሞክራሲ ባህልን ማሳደግ ምክር ቤቱ ትኩረት የሚሰጣቸው ተግባራት እንደሆኑ አንስተዋል። የአፍሪካ ህብረት እ.አ.አ ሐምሌ 9/2002 በደቡብ አፍሪካ ደርባን ባካሄደው የመጀመሪያ ጉባኤ የሰላምና ፀጥታ ምክር ቤት ማቋቋሚያ ፕሮቶኮልን ማጽደቁ ይታወቃል። ፕሮቶኮሉ ከታህሳስ 2003 ጀምሮ በከፊል ሲተገበር ቆይቶ ከ2004 የመጀመሪያዎቹ ወራት አንስቶ ሙሉ ለሙሉ ወደ ስራ ገብቷል። የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ጸጥታ ምክር ቤት እኩል ድምጽ ያላቸው 15 አባል አገራትን የያዘ ሲሆን በአህጉሪቱ ሰላምና ጸጥታ ጉዳይ ላይ የሚሰራ ነው።
ኖርዌይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለመጠቀም የምታካሂደው እንቅስቃሴ በዘርፉ ፈርቀዳጅ ሀገር ሊያደርጋት ይችላል ተባለ
Apr 3, 2024 359
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 25/2016(ኢዜአ)፡- ኖርዌይ በኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ረገድ የምታከናውነው ተግባር ተሽከርካሪዎቹን በስፋት በመጠቀም ቀዳሚዋ ሀገር ሊያደርጋት እንደሚችል ተገለጸ። ኖርዌይ ከአውሮፓውያኑ 2025 ጀምሮ የናፍጣና የቤንዚን ተሽከርካሪዎች ወደ ሀገሪቱ እንዳይገቡ ክልከላ ማድረጓ ተዘግቧል። የሃገሪቱ ዜጎች የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን እንዲጠቀሙ ከፍ ያሉ ማበረታቻዎች እየተደረገላቸው እንደሚገኝ ነው የተዘገበው።   የነዳጅ ተሽከርካሪዎች በሃገሪቱ ላይ ከፍ ያለ የአካባቢና የአየር ብክለት ማስከተላቸው ለዚህ ውሳኔ ገፊ ምክንያት መሆኑን የገለጸው የኖርዌይ መንግስት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች በስፋት በዜጎች እንዲዘወተሩ ለማድረግም ከፍተኛ የተባለ የግብር ቅነሳ አድርጓል። የግብር ቅነሳና መሰል ማበረታቻዎች ትርጉም ያለው ለውጥ በማምጣታቸው በሃገሪቱ ጥቅም ላይ ከዋሉት ተሽከርካሪዎች አብዛኞቹ የኤሌክትሪክ ሆነዋል ሲል ዘኢንዲፔንደት ዝግቧል። በሀገሪቱ የሚገኙትን የናፍጣና የቤንዚን ተሽከርካሪዎች ሙሉ ለሙሉ በኤሌክትሪክ ተክቶ ለማጠናቀቅ ጥቂት አመታት መውሰዱ እንደማይቀር በዘገባው ተመልክቷል። የመንግስት ቁርጠኝነት በዚሁ ከቀጠለ ሁሉም የሃገሪቱ ዜጎች የሚጠቀሙባቸው ተሽከርካሪዎች ሙሉ ሙሉ በኤሌክትሪክ የሚተኩ መሆኑን ነው ዘገባው ያተተው። በኖርዌይ የልሂቃን ቡድን የመጓጓዣ ዘርፍ ተመራማሪ ኢንግቪልር ሮርሆልት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ሽያጭ ከ92 በመቶ በላይ ማደጉን አስረድተዋል።   ኖርዌይ የወሰደችው አይነት እርምጃ በሌሎች ሃገራት መተግበር ቢችል አሁን ያለው የነዳጅ ዋጋ ሊረጋጋ ከመቻሉም በላይ የአየርና የአካባቢ ብክለትም ሊቀንስ እንደሚችል ተመልክቷል። ባሳለፍነው የአውሮፓውያን አመት በሃገሪቱ 1 መቶ 5 ሺህ የኤሌክትሪክ እና 76 ሺህ የነዳጅ ተሽከርካሪዎች ተሽጠዋል ተብሏል።
በደቡብ ምስራቅ ብራዚል በጣለ ከባድ ዝናብ በትንሹ ሰባት ሰዎች መሞታቸው ተገለጸ
Mar 25, 2024 522
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2016(ኢዜአ)፦በደቡብ ምስራቅ ብራዚል በጣለ ከባድ ዝናብ በትንሹ ሰባት ሰዎች መሞታቸው ተገልጿል። ከሬዮዴጄኔሮ 65 ኪሎ ሜትሮችን በምትርቀው ፔትሮ ፖሊስ በደረሰው አደጋ በትንሹ ሰባት ሰዎች መሞታቸውንና በርካቶች መቁሰላቸውን የአካባቢው ባለስልጣናት ገልጸዋል። በአደጋው ለ16 ሰዓታት ያክል በጭቃ ተሸፍና ህይወቷን ማትረፍ የተቻለ የአራት ዓመት ታዳጊን ጨምሮ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች ዝናቡን ተከትሎ ከተከሰተው የመሬት መንሸራተት ከ100 በላይ ሰዎችን ማዳናቸውም ተገልጿል። መቀመጫውን በሰሜን አሜሪካ ያደረገው ፒቢኤስ(public broadcasting service) እንደዘገበው ረዘም ላለ ሰዓት በጣለው ዝናብ ምክንያት በከተማዋ የመሬት መንሸራተትን ጨምሮ ቤቶችም ፈራርሰዋል። የከተማው ከንቲባ ክላውዲዮ ካስትሮ እንደገለጹት ካለፈው ሀሙስ ጀምሮ አደጋው ሊከሰት እንደሚችልና ነዋሪዎቹም እንዲጠነቀቁ መልዕክት ተላልፏል። የአደጋ ጊዜ ሰራተኞችም በአደጋው ጉዳት የደረሰባቸውን ዜጎች ለማዳን በአነፍናፊ ውሾች ጭምር በመታገዝ የነፍስ አድን ስራዎችን እያከናወኑ ሲሆን እስከ አሁን አንድ ሰው የደረሰበት እንዳልታወቀ ተገልጿል። የአየር ትንበያ ባለሙያዎች በፔትሮፖሊስ የተከሰተው ከባድ ዝናብ ኤስፒሪቶ ሳንቶ ወደተባለው አጉራባች ክልል ሊገባ እንደሚችልና አስፈላጊው ጥንቃቄ እንዲደረግ አሳስበዋል።
የቻይና- አፍሪካ የንግድ ልውውጥ ዕድገት  
Mar 14, 2024 843
የቻይና አፍሪካ ግንኙነት ባለፉት አስርት አመታት በከፍተኛ ደረጃ እያደገ በመምጣቱ ቻይና በአፍሪካ አህጉር በንግድ፣ በኢንቨስትመንት እና በመሠረተ ልማት ዝርጋታ ዋነኛ ተዋናይ ከሆኑ ሀገራት መካከል አንዷ አድርጓታል። በቻይና እና በአፍሪካ ሀገራት መካከል ያለው የንግድ ልውውጥ በተያዘው የፈረንጆች ዓመት ከ47 ቢሊዮን ዶላር በላይ መድረሱን የስፑትኒክ ዘገባ ያመለክታል። የንግድ ልውውጡ በፈረንጆቹ አዲስ ዓመት የመጀመሪያዎቹ ሁለት ወራት ብቻ በ13.9 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። ቻይና ወደ አፍሪካ የምትልከው ምርት በ21 በመቶ ማደጉን ያመለከተው ስፑትኒክ በአንፃሩ ቻይና ከአፍሪካ ሀገራት የምታስገባው ምርት መጠን በ4.5 በመቶ ዕድገት አሳይቷል። በፈረንጆቹ 2021 ይፋ የሆነው የቻይና አፍሪካ ትብብር ራዕይ 2035፤ "በአፍሪካ የተሰራ" የሚሉ ብራንዶችን በመፍጠር እና በማቋቋም ረገድ የአፍሪካ ምርቶች በዓለም ገቢያ ተመራጭ እንዲሆኑ ቻይና እየሠራች እንደሆነ ዘገባው አመልክቷል። የቻይና አፍሪካ 2035 ራዕይ አፍሪካ የማኑፋክቸሪንግ ዘርፉን እንድታሳድግ እና ከአለም አቀፍ የኢንዱስትሪ እና የአቅርቦት ሰንሰለት ጋር እንድትተሳሰር ለማድረግ እቅድ እንዳለውም በዘገባው ተጠቁሟል። ባሳለፍነው የፈረንጆቹ 2023 መገባደጃ ላይ ቻይና ኢትዮጵያን ጨምሮ ስድስት የአፍሪካ ሀገራት ምርቶቻቸውን ከቀረጥ ነፃ ወደ ሀገሯ እንዲገቡ መፍቀዷን ያስታወሰው ዘገባው፤ ይህም የአፍሪካ ቻይና የንግድ ትስስርንና ትብብርን ከፍ እንዲል አድርጓል ብሏል። ከአፍሪካ ሀገራት ደቡብ አፍሪካ የቻይና ትልቁ የንግድ አጋር መሆኗን ያመለከተው ዘገባው፤ ናይጄሪያ፣ አንጎላ እና ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እንደቅደም ተከተላቸው የቻይና የንግድ አጋር መሆናቸውን መረጃው ያመለክታል።  
በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎች በኢትዮጵያ 
Mar 14, 2024 896
ወደ ሀገር ውስጥ የሚገባውን የነዳጅ ፍጆታ ለመቀነስ እና የአየር ብክለትን ለመከላከል የሚደረገውን ሰፊ ጥረት እውን ለማድረግ ኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለህዝብ ማመላለሻ አገልግሎት በማዋል ከፍተኛ እምርታን አስመዝግባለች ይላል የአፍሪካ 24 ድረ ገጽ ዘገባ። በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ላይ እየተዘዋወሩ የሚገኙት የኤሌክትሪክ ሚኒባሶች ድምጽ አልባና ለአካባቢው ተስማሚ መሆናቸውን ያተተው የአፍሪካ 24 ድረ ገጽ ዘገባ፤ ይህ የለውጥ ጅማሮ እየጨመረ በመጣው ፍላጎት እና በመንግስት ጠንካራ ድጋፍ የተገኘ መሆኑን አመልክቷል። መንግስት በነዳጅ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን በረጅም የጊዜ ማእቀፍ ውስጥ ከጎዳናዎች የማስወጣት እቅድ ነድፎ እየሰራበት በመሆኑ ምክንያት አሮጌዎቹን የነዳጅ ተሽከርካሪዎች ተክተው ለዜጎች ንጹህና ጤናማ አገልግሎት የሚሰጡት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ከፍ ያሉ ማበረታቻዎች እየተደረገላቸው መሆኑንም ዘገባው አመልክቷል። ከእነዚህ ማበረታቻዎች መካከልም ለአካባቢ ጥበቃና ለጤና ምቹ ናቸው የተባሉት በኤሌክትሪክ የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ያለምንም ቀረጥ አሊያም በዝቅተኛ ቀረጥ ወደ ሀገር ውስጥ እንዲገቡ ወይም በከፊል ገብተው እንገጣጠሙ ማድረግ ተጠቃሽ ነው። እነዚህ ተሽከርካሪዎች ሃገር ውስጥ ገብተው መገጣጠማቸው ለኢትዮጵያውያን የእውቀትና የሙያ ሽግግር ከማድረጋቸው ባለፈ ለወጣት ክፍል የስራ እድሎችን እንደሚፈጥሩ ዘገባው አመልክቷል። በሃገር ውስጥ የተገጣጠሙት ተሽከርካሪዎች የዜጎችን እንቅስቃሴ ከማሳለጥ አኳያም ጉልህ አበርክቶ እንዳላቸውም ጠቁሟል። የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች መስፋፋት ለነዳጅ ግዥ የሚወጣውን ከፍተኛ የሃገር ሃብት ለሌላ ልማት ለማዋልና ከአካባቢ ጥበቃና ከዜጎች ጤና ጋር በተያያዘ የኢትዮጵያ መንግስት ያለውን ቁርጠኝነት ያሳየበት መሆኑን ያነሳው ዘገባው ተሽከርካሪዎቹ በስፋት ጥቅም ላይ ሲውሉ የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ከማሻሻላቸውም ባሻገር ጤናማ የከተሞች ውስጥ እንቅስቀሴ በመፍጠር የአረንጓዴ አሻራ ትልሙን በማሳካት ያግዛሉ ብሏል።
በህንድ አንድ እቃ ጫኝ ባቡር ያለ አሽከርካሪ 70 ኪሎ ሜትሮች መጓዙ ተነገረ
Feb 26, 2024 1260
አዲስ አበባ ፤የካቲት 18/2016 (ኢዜአ)፦በህንድ አንድ እቃ ጫኝ ባቡር ያለ አሽከርካሪ 70 ኪሎ ሜትሮች መጓዙን ተከትሎ የሀገሪቱ የባቡር አስተዳደር ምርመራ እያካሄደ መሆኑን ገልጿል። በህንድ አንድ እቃ ጫኝ ባቡር ያለ አሽከርካሪ መንቀሳቀሱን የሚያሳዩ ምስሎች በማህበራዊ ሚዲያ መሰራጨታቸውን ተከትሎ ጉዳዩ አነጋጋሪ ሆኗል። የህንድ የባቡር አስተዳደር ባለስልጣናት ለመገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ መነሻውን ከካሽሚር ግዛት ወደ ጃሙ ያደረገ እቃ ጫኝ ባቡር ያለ አሽከርካሪ እሁድ ከቀኑ 7፡15 እስከ ቀኑ 9 ሰዓት ድረስ መጓዙን ተናግረዋል። በ53 ፍርጎዎች ለቤትና መንገድ ግንባታ የሚያገለግሉ የድንጋይ ጠጠሮችን ጭኖ ሲጓዝ የነበረው ባቡሩ በሰዓት 100 ኪሎ ሜትር ፍጥነት እንደነበረውም ተነግሯል። ሆኖም በሰው ህይወት ላይ ምንም አይነት ጉዳት ሳያደርስ ባቡሩን ማስቆም እንደተቻለ ነው ሃላፊዎቹ የገለጹት። በካቱሃ ግዛት የአሽከርካሪዎችና ባለሙያዎች ቅይይር ሲደረግ ችግሩ ሊፈጠር እንደቻለ የተነገረ ሲሆን 70 ኪሎ ሜትሮችን ያለ አሽከርካሪ እንዴት ሊጓዝ ቻለ የሚለው ጉዳይ ላይ በጥብቅ ምርመራ እንደሚደረግ ቢቢሲ ዘግቧል። የቁጥጥር ባለሙያዎች ባቡሩን ለማስቆም የዛፍ ግንዶች እንደተጠቀሙ ያስነበበው ዘገባው በዚህም የባቡሩን ፍጥነት በመቀነስና በካቱሃ ግዛት እንዲቆም መደረጉን አስነብቧል።
የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም የኢትዮጵያ ድል በአፍሪካ ታሪክ ጉልህ ስፍራ እንዳለው ማሳያ ነው
Feb 17, 2024 1510
አዲስ አበባ፤ የካቲት 9/2016(ኢዜአ)፡- የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም የኢትዮጵያን ድል የሚዘክር እና ድሉ በአፍሪካ ታሪክ ውስጥ አገሪቱ ያላትን ጉልህ ስፍራ የሚያሳይ መሆኑ ተገለጸ። የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን ከ128 ዓመታት በፊት በአንድነት ተሰልፈው ድል በመንሳት ነፃነታቸውን ያስከበሩበት መሆኑን ሩሲያ የዜና አገልግሎት ስፑትኒክ ዘግቧል። ስፑትኒክ የአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም ምረቃን አስመልክቶ ከአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አማካሪ ልደት ሙለታ ጋር ቃለምልልስ አድርጓል። በዚሁ ቃለምልልስ ላይ ልደት ሙለታ ሙዚየሙ በመሀል አዲስ አበባ ላይ እንዲገነባ የተወሰነው ቦታው ለመላው ኢትዮጵያውያን ካለው ታሪካዊ ፋይዳ አንጻር መሆኑን አስረድተዋል። ሙዚየሙ የተገነባበት ቦታ ኢትዮጵያውያን ወደ አድዋ ከመዝመታቸው በፊት ከሁሉም የአገሪቱ አቅጣጫዎች በመትመም የተሰበሰቡበት መሆኑን አማካሪዋ አስገንዝበዋል። መታሰቢያ ሙዚየሙ የኢትዮጵያውያን የአንድነት ምልክት ሆኖ ከማገልገሉም በተጨማሪ የአድዋ ድል መነሻ መሆኑንም ያሳያል ብለዋል። በዚህ ታሪካዊ የአDዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም በርካታ ታሪካዊ ቅርሶች የያዘ መሆኑን ያስረዱት ልደት ሙለታ ከእነዚህ መካከል በጠንካራ ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ከተሰረቀበት ጣሊያን አገር እንዲመለስ የተደረገው እ.አ.አ በ1935 ኢትዮጵያውያን ከጀርመን ኢንጂነሮች ጋር በመተባበር የሰሩት የመጀመሪያ የኢትዮጵያ አውሮፕላን እንደሚገኝበት አስረድተዋል። አማካሪዋ ከአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም መገንባት ማዕከላዊ ሀሳቦች መካከል አንዱ ኢትዮጵያ በቅኝ ግዛት ወረራ ያሳየችውን ተቃውሞና አልገዛም ባይነት ለማስታወስ እና የሀገሪቱን ድል ለመዘከር ነው ብለዋል። ሁሉን አቀፍና አካታች የሆኑ ቀጠናዊና ዓለም አቀፋዊ ትብብሮችን በስፋት መጠቀም እንደሚያስፈልግ ያብራሩት አማካሪዋ ጂኦ ፖለቲካል አሰላለፎችን በመገንዘብ የታዳጊ ሀገራትን ድምጽ የሚያጎሉ ቁልፍ ዓለም አቀፍ መድረኮችን መጠቀም እንደሚገባም ጠቁመዋል። አማካሪዋ አክለውም፤ ኢትዮጵያ በቅርብ ጊዜ በብሪክስ (BRICS) ውስጥ በአባልነት መካተቷ በአለም አቀፍ ዲፕሎማሲ እና በአለም ዙሪያ ካሉ አገራት ጋር በሚደረገው የትብብር ሂደት እያደገ የመጣውን ተጽእኖ ፈጣሪነቷ ያሳያል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም