ፖለቲካ
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ የተለያዩ ሹመቶችን በማጽደቅ ተጠናቀቀ
Jul 12, 2025 11
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ጉባኤ የተለያዩ ሹመቶችን በማጽደቅ ተጠናቋል፡፡ ምክር ቤት ለሁለት ቀናት ባካሄደው መደበኛ ጉባኤው የከተማ አስተዳደሩ የ2017 በጀት ዓመት ሪፖርት፣ የ2018 በጀት ዓመት አቅጣጫ፣ የ2018 ረቂቅ በጀት እና የተለያዩ አዋጆች ላይ በመወያየት አጽድቋል።   በተጨማሪም በአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የቀረቡ የተለያዩ ተቋማት ሃላፊዎችን ሹመት አጽድቋል። በዚህም መሰረት አቶ አብዱልቃድር ሬድዋን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ፣ አቶ መኮንን ያኢ የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ሃላፊ፣ አቶ ኦሊያድ ስዩም የከተማ ቦታ ማስለቀቅ ጉዳዩች እና ይግባኝ ሰሚ ጉባኤ ፕሬዝዳንት ሆነው ተሹመዋል። ምክር ቤቱ የአስፈፃሚ አካላት ስልጣንና ተግባር እንደገና ለመወሰን የቀረበውን ረቂቅ የማሻሻያ አዋጅ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል። የማሻሻያ ረቂቅ አዋጁ ውሳኔ፣ አስፈላጊነት፣ ዝርዝር ይዘት፣ ተሳትፎ፣ የሚያስገኘው ሃብት፣ የሚፈታው ችግር እንዲሁም ለከተማዋ ሁለንተናዊ እድገት ያለውን ተገቢነት ታሳቢ በማድረግ የተዘጋጀ መሆኑ ተገልጿል።   በዚህም መሠረት፦ - ከአዲስ አበባ የባህል ኪነ ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ተልዕኮዎች የቱሪዝም ዘርፉ ለብቻው የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽን ሆኖ ለከንቲባ ፅህፈት ቤት ተጠሪ በመሆን እንዲቋቋም፣ - የአዲስ አበባ ዲዛይንና ግንባታ ቢሮን ከትላልቅ ፕሮጀክቶች ግንባታ ፅህፈት ቤት ጋር እንዲዋሃድ፣ - የአዲስ አበባ ማህበራዊ ትረስት ፈንድ ፅህፈት ቤት ከህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፍቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ጋር እንዲዋሃድ እና - የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ አንድ ተግባር በከፊል ለውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ማስተላለፍ ላይ የቀረበውን ማሻሻያ አዋጅ ምክር ቤቱ በመሉ ድምፅ አፅድቋል።
የመከላከያ ዩኒቨርሲቲ ብቁ ሰራዊት ከመገንባት በተጓዳኝ ወታደራዊ ቴክኖሎጂዎችን እየፈጠረ ነው - ብርጋዴር ጀነራል ከበደ ረጋሳ
Jul 12, 2025 72
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ብቁ ሰራዊት ከመገንባት በተጓዳኝ ዘመኑን የዋጁ ወታደራዊ ቴክኖሎጂዎች እየፈጠረ እንደሚገኝ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ብርጋዴር ጀነራል ከበደ ረጋሳ ገለጹ። ዩኒቨርሲቲው በምህንድስና፣ በጤና ሳይንስ፣ በቢዝነስ፣ በኃብት አስተዳደር እና በሌሎች የትምህርት መርኃ ግብሮች በመጀመሪያ፣ በሁለተኛ እና በሶስተኛ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ዛሬ አስመርቋል።   በምረቃ መርኃ ግብሩ የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሐመድ፣ የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ(ዶ/ር)፣ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ እና የዩኒቨርሲቲው ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ፣ የመከላከያ ከፍተኛ መኮንኖች፣ የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎችና የተመራቂ ቤተሰቦች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ብርጋዴር ጄኔራል ከበደ ረጋሳ፤ ዩኒቨርሲቲው በተለያዩ የትምህርት መስኮች ወታደራዊ፣ ሲቪል እና የጎረቤት ሀገራት ተማሪዎችን በማሰልጠን ላይ ይገኛል ብለዋል። በዚህም ዩኒቨርሲቲው በእውቀትና በክህሎት ብቁ የሆነ የሰው ኃይል እያፈራ መሆኑንም ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲው የመከላከያ ሰራዊቱን የተልዕኮ አፈጻጸም ወደ ላቀ ደረጃ የሚያደርሱ ወታደራዊና ሲቪል አመራሮችን በማፍራት ላይ እንደሚገኝም ገልጸዋል።   በቴክኖሎጂው ዘርፍ ሀገርን የሚያሻግሩ ሥራዎች በመስራት ላይ እንደሚገኝ ጠቁመው የመከላከያን የሰለጠነ የሰራዊት ግንባታ በማገዝ ላይ መሆኑንም ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲው የሰራዊቱን ስምና ዝና በሚመጥን መልኩ የተዋቀረ ሲሆን ከመማር ማስተማር ስራዎች በተጓዳኝ የተለያዩ የጥናትና ምርምር ስራዎችና ሌሎች ህብረተሰቡን የሚጠቅሙ ተግባራት እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ዘመናዊ ሰራዊት ለመገንባት ከውጭ የምታስገባቸውን ቴክኖሎጂዎች በሀገር ውስጥ ለመተካት ዩኒቨርሲቲው የተለያዩ ስራዎችን በመሥራት ላይ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል። ተመራቂዎች ባገኙት እውቀትና ከፍተኛ ክህሎት ሀገራቸውን በብቃት ማገልገል እንደሚገባቸው መልዕክት አስተላልፈዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ በ2025 ከአፍሪካ አምስት ምርጥ የመከላከያ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ የመሆን ራዕይ ሰንቋል።
የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ አሰራሩን በቴክኖሎጂ ለማስደገፍ የጀመራቸውን ተግባራት አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል - ቋሚ ኮሚቴው
Jul 11, 2025 125
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ አሰራሩን በቴክኖሎጂ ለማስደገፍ የጀመራቸውን ተግባራት አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። ቋሚ ኮሚቴው በተሻሻለው የኢትዮጵያ ምርጫ፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ ምግባር ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ የውይይት መድረክ አካሂዷል። በውይይት መድረኩ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችና ማህበራት፣ መገናኛ ብዙሃን ኃላፊዎችን ጨምሮ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል። አዋጁ በምርጫ ጣቢያ ደረጃ የሚቀርብ ማንኛውም ቅሬታ በምርጫ ጣቢያ ኃላፊ ታይቶ ውሳኔ እንዲሰጥበት የሚደነግግ ሲሆን የምርጫ ክልል አቤቱታ ሰሚ ኮሚቴ አባላት ከዚህ በፊት ከህብረተሰቡ ይመደብ የነበረው ቀርቶ ቦርዱ አሰልጥኖ በሚመድባቸው የምርጫ አስፈጻሚዎች እንዲተኩ የሚያደርግ ነው። ከዚህ ቀደም በነበረው አዋጅ አንድ ፓርቲ ሀገራዊ ፓርቲ ሆኖ ለመመዝገብ የሚመለምለው አባል ከ5 ክልሎች የነበረ ሲሆን በተሻሻለው አዋጅ አንድ ፓርቲ አባላትን መመልመል ያለበት ከ7 ክልሎች ሊሆን እንደሚገባም በአዋጁ ተመላክቷል። አንድ ፓርቲ ከመንግሥት ድጋፍ ለማግኘት ከ30 በመቶ ከሚሆነው አባሉ የአባልነት መዋጮ መሰብሰብ እንደቅደመ ሁኔታም ተቀምጧል። በአዋጁ መሰረት ጥሰት ፈጽመው የተገኙ ፓርቲዎች እስከ አምስት ዓመት ድረስ ሊታገዱ የሚችሉበት ድንጋጌም ከተካተቱ ጉዳዮች መካከል ነው። በውይይቱ ከተሳተፉ መካከል የቦሮ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ተወካይ መብራቱ ዓለሙ(ዶ/ር) በሰጡት አስተያየት፤ በምርጫ ጣቢያ ለሚቀርቡ ጥያቄዎች የምርጫ ጣቢያ ኃላፊ አይቶ ውሳኔ ይሰጣል የሚለው የአንቀጹ ክፍል ለአተገባበር አስቸጋሪ ሊሆን ይችላል ብለዋል።   የቁጫ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ተወካይ ባንዲራ በላቸው እንደገለጹት፤ ፓርቲዎች 30 በመቶ መዋጮ እንዲያሰባስቡ የተቀመጠው ድንጋጌ ከነባራዊ ሁኔታ አኳያ ተግባራዊ ሊሆን ይችላል ወይ የሚለው ሊጤን እንደሚገባ ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌደሬሽን ዋና ዳይሬክተር አባይነህ ጉጆ በበኩላቸው በአዋጁ የአካል ጉዳተኞችን ተሳትፎ የሚያጎለብቱ ድንጋጌዎች ሊካተቱ ይገባል ብለዋል።   የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሜላተወርቅ ኃይሌ በሰጡት ማብራሪያ በአዋጁ ፓርቲዎች 30 በመቶ ያህል መዋጮ ከአባላት ሊሰበሰቡ እንደሚገባ የተደነገገው ፓርቲዎች በመንግሥት በጀት ላይ ብቻ እንዳይመሰረቱና ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ ነው ብለዋል። አዋጁ አካል ጉዳተኞችንና ሴቶችን አካታች በሆነና ተሳትፏቸውን በሚያሳድግ መልኩ መቃኘቱን አንስተዋል። የመንግሥት ሰራተኞች በምርጫ ውድድር ወቅት ደሞዛቸውን ይዘው እንዲሳተፉ መደረጉ ለፖለቲካ ምህዳሩ ትልቅ እርምጃ መሆኑን አብራርተዋል።   የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ተስፋዬ ነዋይ በሰጡት ማብራሪያ፤ በምርጫ ጣቢያ ደረጃ የሚነሱ ቅሬታዎች በምርጫ ጣቢያ ኃላፊ እንዲፈታ አቅጣጫ የተቀመጠው ፈጣን ምላሽ ለመስጠት ታልሞ መሆኑን አስረድተዋል። እንዲያም ሆኖ ቅሬታዬ አልተፈታም የሚል ማንኛውም አካል ጥያቄውን በየደረጃው የሚያቀርብበት አሰራር መዘርጋቱን ጠቁመዋል።   በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አዝመራ አንደሞ በበኩላቸው በህዝባዊ የውይይት መድረኩ የተነሱ ሀሳቦች ለአዋጁ ውሳኔ ሀሳብ የሚረዱ ግበዓቶች የተገኙበት ነው ብለዋል። በቀጣይም ሀገራዊ ምክክር ላይ የፓርቲዎች ተሳትፎ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አመልክተዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እውነቱ አለነ በበኩላቸው ፓርቲዎች የወጣቶችን፣ የአካል ጉዳተኞችንና የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ የበለጠ ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአባልነት መዋጮን በተመለከተም ፓርቲዎች አባላቶቻቸውን ሊያበረታቱ እንደሚገባም ነው የተናገሩት። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ቴክኖሎጂን ስራ ላይ ለማዋል የጀመራቸውን ተግባራት ሊያጠናክር እንደሚገባ ጠቁመው ፓርቲዎችም ይሄንኑ ስራ ሊደግፉ እንደሚገባ አመልክተዋል።
መጪው ምርጫ የትብብርና ፋክክር የዲሞክራሲ ባህል የሚገነባበት እንዲሆን በትኩረት ይሰራል - አቶ ፍቃዱ ተሰማ
Jul 11, 2025 83
ጎንደር፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ መጪው ምርጫ የትብብርና ፋክክር የዲሞክራሲ ባህል የሚገነባበት እንዲሆን በትኩረት እንደሚሰራ የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ፍቃዱ ተሰማ ገለጹ። ከተለያዩ የሀገሪቱ ክልሎች የተውጣጡ የፓርቲው የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊዎች የተሳተፉበትና በጎንደር ከተማ ለሁለት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የግምገማ መድረክ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ ማምሻውን ተጠናቋል። አቶ ፍቃዱ ተሰማ የግምገማ መድረኩ ማጠቃለያን አስመልክተው በሰጡት መግለጫ፤ ፓርቲው መጪው ምርጫ ስኬታማ እንዲሆን መላ አባላቱን የማዘጋጀት ስራዎቹን በትኩረት ያከናውናል ብለዋል። ለዚህም የአባላት የስነ-ምግባር ደንቦችን በማዘጋጀት በምርጫው የትብብርና ፉክክር ዴሞክራሲያዊ ባህል እንዲዳብር እንደሚሰራም ተናግረዋል። አባላቱ በፓርቲው እሳቤዎች፣ መተዳደሪያ ደንብና አሰራሮች ዙሪያ ወጥና የተቀራረበ ግንዛቤ በመያዝ ተቋማዊ ተልዕኳቸውን በብቃት እንዲወጡ አቅማቸውን የመገንባት ስራ ይከናወናል ብለዋል። የፓርቲው አደረጃጀቶች በልማት በሠላምና በመልካም አስተዳደር ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤቶችን ለማስቀጠል እንደሚሰሩም ጠቁመዋል። የተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሀገር አቀፍ ደረጃ እንደፓርቲና መንግስት ሰፋ ያሉ ውጤቶች የተመዘገቡበትና የማንሰራራት ዘመን በተጨባጭ የታየበት መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ዓመቱ በፓርቲው ውስጥ የአመለካከት፣ የተግባር አንድነትና ህብረ ብሔራዊነት የተጠናከረበት እንደነበርም ተናግረዋል። ከተረጂነት ለመላቀቅ በሚደረገው ጥረት በጎ ጅምር የታየበት፣ ኢኮኖሚያዊ እድገቱ የሀገሪቱን በጀት በትሪሊዮን እንዲጸድቅ ያስቻለና የእዳ ቅነሳ የተደረገበት መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ የአረንጓዴ አሻራና የከተሞች ኮሪደር ልማት ፕሮጀክቶች አፈጻጸም ውጤታማ እንደነበርም አብራርተዋል፡፡ በሠላም ማስከበር ሂደቱ የታጠቁ ኃይሎች የመንግስትን የሠላም አማራጭ ተቀብለው ተሃድሶ በመውሰድ በስፋት ወደ ሠላማዊ ህይወት መመለሳቸውንም አስታውሰዋል። በቀጣይም ሀገራዊ ምክክሩ እንዲሳካ ፓርቲው የበኩሉን ድጋፍ እንደሚያደርግ ኃላፊው አረጋግጠዋል።
የከተማዋን ሰላም በዘላቂነት ለማስቀጠል ወጣቶች ተሳትፏቸውን ማጠናከር ይጠበቅባቸዋል
Jul 11, 2025 47
ወልዲያ ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፡- የወልዲያ ከተማን ሰላም አፅንቶ በዘላቂነት ለማስቀጠል ወጣቶች ተሳትፏቸውን ማጠናከር እንደሚጠበቅባቸው የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራሬ ገለጹ። የከተማ አስተዳደሩ ከከተማው ወጣቶች ጋር በሰላምና ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ የምክክር መድረክ ዛሬ አካሂዷል።   በመድረኩ ላይ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራሬ እንዳሉት፤ የአካባቢን ሠላም ለማፅናት ወጣቱ ከፀጥታ አካላት ጋር በመተባበር የድርሻውን ሲወጣ ቆይቷል። በዚህም የህግ የበላይነትን በማስከበር ሰላም ማስፈን መቻሉን ገልጸው፤ የተገኘውን ሰላም አስጠብቆ ዘላቂ ለማድረግ ወጣቶች ሲያበረክቱ የቆዩትን አስተዋጽኦ ማጠናከር እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል። በሰሜን ምስራቅ ዕዝ የ801ኛ ኮር አዛዥ ብርጋዴር ጄኔራል ዘውዱ ሰጥአርጌ በበኩላቸው፤ የመከላከያ ሰራዊቱ ከህብረተሰቡ ጋር በመተባበር የህግ የበላይነት ተከብሮ ሰላም ለማፅናት ውጤታማ ስራዎች ማከናወኑን ገልጸዋል። የወልዲያ ከተማ ወጣቶች ጽንፈኛውን አጥብቀው በመታገል ሲያበረክቱት የቆዩትን አስተዋጽኦ ይበልጥ አጠናክረው እንዲቀጥሉም መልዕክት አስተላልፈዋል። በውይይቱ የተሳተፉ ወጣቶች የአካባቢያቸውን ሰላም ለማስከበር ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል። በምክክር መድረኩ ላይ ከከተማዋ የተወጣጡ ወጣቶችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በበጀት አመቱ በከተማዋ በተከናወኑ ስኬታማ የሰላም ተግባራት የህብረተሰቡ ተሳትፎ ከፍተኛ ነበር - የከተማዋ የምክር ቤት አባላት
Jul 11, 2025 81
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ በበጀት አመቱ በከተማዋ በተከናወኑ ስኬታማ የሰላም ተግባራት የህብረተሰቡ ተሳትፎ ከፍተኛ እንደነበር የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አባላት ተናገሩ። 3ኛው የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ እና የበጀት አመቱ ማጠቃለያ ስብሰባ እየተካሄደ ነው። በስብሰባው ከንቲባ አዳነች አቤቤ የ2017 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት እና የ2018 በጀት ዓመት ዋና ዋና አቅጣጫዎችን ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። በዚሁ ጊዜ በ2017 በጀት ዓመት የከተማዋን ሰላም በማስጠበቅ፣ የነዋሪዎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ከማሳደግ እንዲሁም አህጉራዊና ዓለም-አቀፋዊ ሁነቶችን በማስተናገድ ስኬታማ ሥራዎች መሰራታቸውን ነው ያብራሩት። በከተማዋ ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ በርካታ የጸጥታና የወንጀል ድርጊቶችን በመለየትና አስቀድሞ በመከላከል ብሎም ህጋዊ እርምጃዎችን መውሰድ መቻሉን አንስተዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት አባላትም የከተማዋን ሰላምና ደህንነት ከማረጋገጥ አንጻር የተከናወኑት ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን ተናግረዋል።   የአዲስ አበባ ከተማ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊና የምክር ቤቱ አባል ሊዲያ ግርማ በበጀት ዓመቱ በከተማዋ ሰላም በመረጋገጡ የልማት ስራዎች ስኬታማ በሆነ መልኩ እንዲከናወኑ በትኩረት መሰራቱን ገልጸዋል። የከተማው ነዋሪ ህብረተሰብም በወንጀል መከላከል ሂደትና ሰላም በማስጠበቅ ሂደት ላይ የነበረው ተሳትፎ በየጊዜው እየጎለበተ መምጣቱን እንዲሁ። ሰላም ለአንድ ሀገር ሁለንተናዊ ልማት የማይተካ ሚና አለው ያሉት ደግሞ ሌላዋ የምክር ቤት አባል ወርቅነሽ ምትኩ (ዶ/ር) ናቸው።   በከተማዋ ለተመዘገቡ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ለውጦች የሰላምና ጸጥታ መረጋገጥ ትልቅ ሚና መጫወቱንም ጨምረው ተናግረዋል፡፡ ሌላው የምክር ቤት አባል ኢቲሳ ደሜ(ዶ/ር) ህዝብን ያሳተፈ የሰላምና ልማት ሥራ የተሻለ ውጤት እንደሚያመጣ አዲስ አበባ ማሳያ ናት ብለዋል።   ከተማዋ የአህጉራዊና አለም አቀፋዊ ተቋማት መቀመጫና የአፍሪካ መዲና በመሆኗ ዘላቂ ሰላምን በማረጋገጥ በኩል ህብረተሰቡ ቀጣይነት ያለው ድጋፉንና ተሳትፎውን ማስቀጠል እንደሚገባ በመጥቀስ። በከተማዋ ሰላምና ልማትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እንዲረጋገጡ የምክር ቤቱ አባላት ድጋፍና ክትትላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጸዋል። የከተማዋን ሰላም በማስቀጠል ሂደትም ነዋሪው ተሳትፎውን አጠናክሮ እንዲቀጥል የምክር ቤት አባላቱ ጥሪ አቅርበዋል።
በህብረብሔራዊ አንድነት ላይ ያተኮረ ትርክት ግንባታ በውጤታማነት ተጠናክሮ ቀጥሏል - ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)
Jul 11, 2025 98
አርባምንጭ ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡-በሀገሪቱ በህብረብሔራዊ አንድነት ላይ ያተኮረ ትርክት ግንባታ በውጤታማነት ተጠናክሮ መቀጠሉን የብልጽግና ፓርቲ የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ሃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ተናገሩ ። የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ የ2017 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2018 ዕቅድ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተገመገመ ነው። የብልጽግና ፓርቲ ዓለም አቀፍና የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ኢትዮጵያ በኢኮኖሚው በፖለቲካውና፣ በዲፕሎማሲው ዘርፍ በዓለም አደባባይ ፈጣን ለውጥ እያስመዘገበች ትገኛለች ብለዋል። ይህን ለማሳካትም የተረጋጋ የፖለቲካ ምህዳር በመፍጠር በህዝቦች መካከል ወንድማማችነትና እህትማማችነት እየተጠናከረ የመጣበት ዓመት ነው ሲሉም ገልጸዋል።   የሀገርን እድገት ወደ ኋላ ለመመለስ የሚጥሩ አካላት በህዝብና በመንግስት ትብብር ሴራቸው እየከሸፈ መምጣቱንም ገልጸዋል። በህብረብሔራዊ አንድነት ላይ ያተኮረ ትርክት ግንባታ ሂደትም ውጤታማ በሆነ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ያነሱት ቢቂላ (ዶ/ር) ''እስካሁን የተመዘገበውን ስኬት ለማስቀጠል አበክረን እንሠራለን'' ብለዋል። በብልጽግና ፓርቲ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ገብረመስቀል ጫላ በበኩላቸው ፓርቲው የህዝቡን ሁለንተናዊ ብልጽግና እያረጋገጠ ይገኛል ብለዋል።   የብሔር ብሔረሰቦችን መብት በማስከበር የተረጋጋች ሀገር የመገንባት ሂደቱም በተሻለ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን አብራርተዋል። በቀጣይም የተጀመሩ ልማቶችን በማስቀጠል የህዝቡን ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሠራ ጠቁመዋል። ለሁለት ቀናት በተዘጋጀው መድረክ ከሁሉም ክልሎች የፓርቲው ህዝብ ግንኙነት ኃላፊዎችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤታማ ስራዎች ወደ ላቀ ደረጃ የማሸጋገሩ ተግባር ይጠናከራል
Jul 10, 2025 121
  ሐረር፤ሐምሌ 3/2017 (ኢዜአ)፡-በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤታማ ስራዎች ወደ ላቀ ደረጃ የማሸጋገሩ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በብልፅግና ፓርቲ የዋና ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለስ ዓለሙ ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ በሐረር ከተማ ለሁለት ቀናት ሲያካሂደው የቆየው የ2017 እቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2018 እቅድ ተግባቦት መድረክ ዛሬ ተጠናቋል። በመድረኩ የፌደራልና የክልል የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ አመራሮች እንዲሁም የፓርቲው የወጣቶችና ሴቶች ክንፍ ተሳትፈዋል። በብልፅግና ፓርቲ የዋና ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለስ ዓለሙ በወቅቱ እንደተናገሩት፥ በ2017 በጀት ዓመት የዴሞክራሲ ባህል እሴትን ለማጠናከር የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል።   የፖለቲካ ፓርቲዎች በትብብር ከመስራት አንጻር በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች በጋራ ምክር ቤቶች በመደራጀት አብሮ የመስራት ባህል እየዳበረ መምጣቱን ጠቅሰዋል። ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የተጀመሩ ስራዎች አዲስ ባህልና ልምድ እያመጡ ስለመሆኑም አንስተዋል። የጋራ ስራዎቹ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸው፤ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ለዴሞክራሲ ባህል ግንባታ በቁርጠኝነት መስራታቸውን አጎልብተው እንዲቀጥሉም አመልክተዋል። በአሁኑ ወቅት በየደረጃው ያለው የመንግስት አካላትና ሲቪል ማህበረሰብ በጋራና በቅንጅት የሚሰሩበት ጅምር ሁኔታ መፈጠሩን ጠቅሰዋል። በተለይ የወጣቶችና ሴቶች አስተዋጽኦን ለማላቅና ተሳትፏቸውን ይበልጥ ለማሳደግ ብሎም ተጠቃሚነታቸውን ለማጎልበት መድረኩ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም አንስተዋል።   በቀጣይም ትኩረት በሚሹ ጉዳዮች ላይ በተቀመጡ አቅጣጫዎች መሰረት ትኩረት ተሰጥቶ እና ባህል አድርጎ እንደሚሰራም አመላክተዋል።
የከተማው ነዋሪዎች ሰላምን ለማፅናት እያበረከቱት ያለው አስተዋጽኦ ለኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት እንቅስቃሴው ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Jul 10, 2025 114
ደብረብርሃን ፤ ሐምሌ 3/ 2017 (ኢዜአ)፡- የደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪዎች ከጸጥታ ሃይሉ ጎን በመሰለፍ በአካባቢው ሰላምን ለማፅናት እያበረከቱት ያለው አስተዋጽኦ ለኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት እንቅስቃሴው ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር በአካባቢው ሰላምን ለማፅናት አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የእውቅና እና የምስጋና መርሃ ግብር አካሂዷል። በመርሃ ግብሩ ላይ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት እንደገለጹት፤ የጸጥታ ሃይሉ ከሕብረተሰቡ ጋር በመተባበር ሰላም እንዲከበር ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል።   በዚህም በከተማዋ የሚካሄዱ የኢንዱስትሪ፣ የኢንቨስትመንትና የንግድ ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ጠቅሰዋል። ይህም ስራ እድል እንዲስፋፋ፣ የገቢና ሌሎች የልማት ዘርፎች ውጤታማ እንዲሆኑ ምቹ መደላድል መፍጠሩን ገልጸዋል። በከተማዋ አሁን ላይ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎች እየተካሄዱ እንደሚገኙ አስረድተዋል። የልማት ሁሉ መሰረት የሆነውን ዘላቂ ሰላም ለማስፈን በሚደረገው ጥረት ሁሉ ሕብረተሰቡ ከጸጥታ ሃይሉ ጎን በመሰለፍ የተለመደ ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥልም መልዕክት አስተላልፈዋል። የእውቅና እና የምስጋና መርሃ ግብሩ ዓላማም የከተማው ነዋሪዎች ከጸጥታ ሃይሉ ጎን በመሰለፍ የህግ ማስከበር ስራው ይበልጥ በውጤታማነት በማስቀጠሉ ሂደት ድጋፋቸውን እንዲያጠናክሩ ለማበረታታ መሆኑን ተናግረዋል።   ከህግ አስከባሪዎች መካከል ሀምሳ አለቃ ሰይፈ ደምሰው በሰጡት አስተያየት፤ ሰላምን አፅንቶ በማስቀጠል ለልማት የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ይበልጥ ለማጠናከር ከሕብረተሰቡ ጋር ተቀናጅተወ በትኩረት እንደሚሰሩ ተናግረዋል። ሌላው የመርሃ ግብሩ ተሳታፊ ፈለቀ በየነ በበኩላቸው፤ የአካባቢውን ሰላም በማፅናት የልማት ስራዎቻቸው ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በቁርጠኝነት እንሰራለን ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የጎዳና ላይ ትርኢቶችና ሌሎች ዝግጅቶች ተካሂደዋል።
በብሔረሰብ አስተዳደሩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል
Jul 10, 2025 98
ሰቆጣ ፤ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት መከናወናቸውን የብሔረሰብ አስተዳደሩ አስታወቀ። የብሔረሰብ አስተዳደሩ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸምን የሚገመግምና የቀጣይ 90 ቀናት ዕቅድ ማስተዋወቂያ መድረክ በሰቆጣ ከተማ እየተካሄደ ነው። የብሔረሰብ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሃይሉ ግርማይ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ ህብረተሰቡን ያሳተፈ የሰላምና ፀጥታ ተግባር በመካሄዱ የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል።   በልማት ሥራም ለመልካም አስተዳደር ምክንያት ሆኖ የቆየው የሰቆጣ አዳሪ ትምህርት ቤትን ጨምሮ የስርዓተ ምግብን ለማሻሻል በዓመት ከ360 ሺህ በላይ ጫጩት ማስፈልፈያ ማዕከል ግንባታ ስራን ማከናወን እንደተቻለ ገልጸዋል። በተጨማሪም የመስኖ መሰረተ ልማትን በማስፋፋት የግብርና ምርታማነት እንዲያድግ መሰራቱን ጠቁመው፣ የመኽር እርሻ ምርታማነትን ለማሳደግም በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በፌደራል፣ በክልልና በወረዳ በጀት እየተገነቡ ያሉ መሰረተ ልማቶች በተቀመጠላቸው ጊዜ በጥራት ተገንብተው እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትሉ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የአመራሩን የማስፈፀም አቅም ይበልጥ በማሳደግ በበጀት ዓመቱ የተገኙ ስኬቶችን በአዲሱ በጀት ዓመትም ለመድገም ከምንጊዜውም በላይ በቁርጠኝነት እንደሚሰራም አቶ ሃይሉ አስረድተዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የፀጥታ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች ጭምር ያልተቋረጠ የጤና አገልግሎት መስጠት መቻሉን የተናገሩት ደግሞ የብሔረሰብ አስተዳደሩ ጤና መምሪያ ሃላፊ አቶ አሰፋ ነጋሽ ናቸው።   በበጀት ዓመቱ በስርዓተ ምግብ ማሻሻል እንዲሁም የወባ እና ሌሎች ተላላፊ በሽታዎችን በመከላከልና በማከም በተሰራው ስራም የከፋ ችግር ሳይደርስ ማለፉንም ተናግረዋል። የእናቶችና ህፃናት ህክምና ማዕከልን ጨምሮ 42 የጤና ፕሮጀክቶች እየተገነቡ መሆናቸውን የተናገሩት አቶ አሰፋ፤ በጤና ተቋማቱ ዜጎችን የጤና አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። የብሄረሰብ አስተዳደሩ የግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ በበኩላቸው "በብሔረሰብ አስተዳደሩ በመስኖ ከለማው መሬት ከ700 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቧል ብለዋል። ይህም የአካባቢውን ገበያ ለማረጋጋት ማገዙን ተናግረዋል።   በበጋው ወቅት በ369 ተፋሰሶች ላይ ህብረተሰቡን ያሳተፈ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ሥራ መካሄዱን ጠቁመው፣ የለሙትን ተፋሰሶች በስነ እፅዋት ዘዴ ለማጠናከርም ችግኞች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። በመድረኩ ላይ የክልል፣ የብሔረሰብ አስተዳደሩና የወረዳ አመራሮች ተሳትፈዋል።
የኢትዮጵያና ዛምቢያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በተለያዩ መስኮች ተጠናክሮ ቀጥሏል - አምባሳደር ሮዝ ሳካላ
Jul 10, 2025 129
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እና በዛምቢያ መካከል ያለው ረጅም ጊዜ ያስቆጠረ ግንኙነት በተለያዩ መስኮች ተጠናክሮ መቀጠሉን በኢትዮጵያ የዛምቢያ አምባሳደር ሮዝ ሳካላ ገለጹ። በኢትዮጵያ የዛምቢያ አምባሳደር ሮዝ ሳካላ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ኢትዮጵያ እና ዛምቢያ ዘላቂ እና ዘርፈ-ብዙ ግንኙነት እንዳላቸው ገለጸዋል። ይህም ግንኙነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ እና በተለያዩ ዘርፎችም እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በተለይም ዛምቢያ ኤምባሲዋን በኢትዮጵያ ከከፈተችበት ጊዜ አንስቶ የሁለቱ አገሮች አጋርነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጎለበተ ከመምጣቱም በላይ የተለያዩ የትብብር ስራዎችም እየተጠናከረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። እ.አ.አ በ2017 ሁለቱ ሀገራት የጋራ ኮሚሽን ማቋቋማቸውን ገልጸው፤ ይህም ተጨባጭ ጥቅሞችን ማስገኘቱን ጠቁመዋል። ሁለቱ ሀገራት ከፍተኛ አቅም እንዳላቸው ገልጸው፤ ከሁለቱም ወገኖች የተውጣጡ የንግድ ባለሙያዎችን እና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን በማሰባሰብ ግንኙነታቸውን የበለጠ ለማሳደግ ጥረት መደረጉን አንስተዋል። የጋራ ኮሚሽኑ በንግድና ኢንቨስትመንት በተለይም በግብርናና በአየር ትራንስፖርት ዘርፍ ያለውን ትስስር እንደሚያጠናክር ጠቁመዋል። ዛምቢያ የአፍሪካን አንድነት ለማጎልበት እና አህጉራዊ አጀንዳዎችን ለማራመድ በተለያዩ መድረኮች በማደራጀት እና በመሳተፍ ንቁ ተሳትፎ እያደረገች መሆኑን ተናግረዋል ። አፍሪካ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውስጥ ቋሚ ውክልና አለማግኘቷ ኢ-ፍትሃዊ ነው ብለዋል። ዛምቢያ ለቀጣናው ኢኮኖሚያዊ ውህደት ትልቅ አስተዋፅዖ እንዳደረገች ገልፀው፤ ፓን አፍሪካኒዝም እንደ መሰረታዊ መርህ እና ከእነዚህ ጥረቶች ጀርባ አንቀሳቃሽ ሃይል ሆኖ ያገለግላል ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ለአፍሪካ በርካታ እድሎችን የሚሰጥ ወርቃማ አጀንዳ መሆኑን ገልጸው፤ በትብብር መተግበር እንደሚገባ አሳስበዋል።
የምርምር ባህልን ማሳደግና ፈጠራን ማበረታታት ቀጣይነት ላለው ሀገራዊ እድገት ወሳኝ ነው-አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ
Jul 10, 2025 113
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ የምርምር ባህልን ማሳደግና ፈጠራን ማበረታታት ቀጣይነት ላለው ሀገራዊ እድገት ወሳኝ መሆኑን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጹ። አምስተኛው ዓመታዊ የፓርላማ ጥናትና ምርምር ኮንፈረንስ "አካታችና ጠንካራ የፓርላማ ስርዓት ለሀገር በቀል እውቀትና ቀጣይነት ላለው ልማት" በሚል መሪ ሀሳብ መካሄድ ጀምሯል።   የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ በጉባኤው መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት፥ በየዓመቱ የሚካሄደው የምርምር ጉባኤ ለእውቀት መፍለቅ፣ለምርምርና ጥናት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው። ጉባኤው ምክር ቤቱ ለተሻለ ህግ ማውጣት፣ ለውጤታማ ክትትልና ቁጥጥር እንዲሁም ለተሳካ የፓርላማ ዲፕሎማሲ የሚያስፈልገውን መረጃና ትንተና እንዲያገኝ እድል መፍጠሩን አስታውሰዋል። በምጣኔ ሃብት፣ፖለቲካ፣ማህበራዊና በቴክኖሎጂ ዘርፎች የሚደረጉ ጥናትና ምርምሮች ሀገራዊ አቅምን ለመገንባትና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ ወሳኝ ናቸው ብለዋል። ምርምር ለማንኛውም አገራዊ ልማትና እድገት መሰረት በመሆኑ በተቋምና በሀገር ደረጃ የላቀ እድገት ለማስመዝገብ ለጥናትና ምርምር ትኩረት መስጠት ተገቢ መሆኑን አስገንዝበዋል። የምርምር ባህልን ማሳደግ፣ፈጠራን ማበረታታትና እውቀትን በተግባር ማዋል ቀጣይነት ላለው እድገት ወሳኝ መሆኑን በመጠቆም በተለይም ለህግ አውጪ አካል ስራዎች የምርምር ሚና የላቀ እንደሆነም ጠቁመዋል። ምክር ቤቱ የሚወስናቸው ውሳኔዎች፣የሚያወጣቸው ህጎችና የሚያደርገው የክትትልና ቁጥጥር ስራ ጥናትና ምርምር ላይ የተመሰረቱ እንዲሆኑ ሚናውን አጠናክሮ ይቀጥላል ያሉት። እንደ አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጻ፥ የሚወጡ ህጎችን ተቀባይነት እንዲኖራቸው በጥናት ላይ የተመሰረተ የህዝብ ፍላጎት፣አስተያየትና ቅሬታን በመሰብሰብና በመተንተን በህግ አወጣጥ ሂደት ውስጥ ማካተት ያስፈልጋል። በተመሳሳይ ምክር ቤቱ መንግስት የሚሰራቸውን ስራዎች ለመከታተል፣ የበጀት አጠቃቀም ለመቆጣጠርና የመንግስት ፖሊሲዎችን ውጤታማነትን ለመገምገም ጥልቅ ትንተና ማድረግ ተገቢ ነው ብለዋል። ምክር ቤቱ ለምርምር ትኩረት በመስጠት፣የምርምር ጉባኤዎችን በማዘጋጀትና የፓርላማ የምርምር ትስስር በማቋቋም ከምርምር ተቋማት ጋር ያለውን ግንኙነት ማጠናከሩንም ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሳሙኤል ክፍሌ(ዶ/ር) በበኩላችው፥ የቴክኖሎጂ ዕድገትን ተከትሎ የተፈጠረው የድህረ እውነት ዓለም አሉታዊ ተጽእኖ እያሳደረ እንደሚገኝ አንስተዋል።   ይህን ለመቀልበስ በጥናት ምርምር ላይ የተመሰረተ ሥራ እና ጠንካራ ፓርላማ መገንባት እንደሚያስፈልግ አመላክተዋል። በምርምር ጉባኤው ጥናታዊ ፅሁፍ ያቀረቡት በጅማ ዩኒቨርሲቲ የማህበራዊ ሳይንስ ተመራማሪ እውነቱ ሃይሉ (ዶ/ር)፥ ኢትዮጵያ ለዘመናት ፀንታ የቆየችው በራሷ ዕውቀትና እውነት ውስጥ በመኖሯ ነው ብለዋል።   ምክር ቤቱ በሚያወጣቸው የህግ ማዕቀፎች ውስጥ ሀገር በቀል እውቀቶችን ማካተት አለበት ያሉት ተመራማሪው፥ የሀገር በቀል እወቀቶችን ፋይዳ ማስገንዘብም እንደሚገባ አስረድተዋል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የህዝብ አስተዳደርና ኢኮኖሚ መምህርና ተመራማሪ ዳንኤል በየራ በበኩላቸው፥ ከሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አካታችነት አንጻር የተገኙ ውጤቶችና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ጥናታዊ ፅሁፍ አቅርበዋል።   ከግሉ ዘርፍ፣ ከትምህርት፣ ከመሰረተ ልማት፣ ከጤና አካታችነት አንጻር ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቅሰው፥ ምክር ቤቱ ለላቀ ስኬት የክትትልና ቁጥጥር ስራውን ማጠናከር እንዳለበት ጠቁመዋል። በአምስተኛው ዓመታዊ የፓርላማ ጥናትና ምርምር ኮንፈረንስ የፓርላማ ዴሞክራሲ ሥርዓት ትግበራ መሻሻል፣የፓርላማ ተግባራትን ማጠናከር፣ የሕግ የበላይት፣አካታች አስተዳደርና ሀገረ መንግሥት ግንባታ ላይ ያተኮሩ 12 የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎች በምሁራን እንደሚቀርቡ የወጣው መርሃ ግብር ያሳያል።
በተለያዩ ሀገራት በችግር ውስጥ የነበሩ ከ131 ሺህ በላይ ዜጎች ተመልሰዋል - የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
Jul 10, 2025 131
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ21 ሀገራት በችግር ወስጥ የነበሩ ከ131 ሺህ በላይ ዜጎች ወደ ሀገራቸው መመለሳቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው ሚኒስቴሩ በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት ዋና ዋና የዲፕሎማሲ ሥራዎችን አስመልክተው ለጋዜጠኞች ማብራሪያ ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ በበጀት ዓመቱ ብሔራዊ ጥቅሟን ያስከበሩ የሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን ግንኙነት በመፍጠር፣ ቀጣናዊ ትስስር እንዲሁም አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ትብብርን ማጠናከር የሚያስችሉ ስኬታማ የዲፕሎማሲ ስራዎች አከናውናለች ብለዋል። ኢትዮጵያ ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት የበለጠ ማጠናከር የሚያስችሉና ቀጣናዊ ትስስርን የሚያፋጥኑ ፍሬያማ የዲፕሎማሲ ተግባራትን ማከናወኗንም አመልክተዋል። ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጋር ተያይዞ የኢትዮጵያን እውነት ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለማስረዳት ጠንካራ የዲፕሎማሲ ሥራዎች መከናወናቸውንም አምባሳደሩ አብራርተዋል። የናይል ተፋሰስ ኮሚሽን እንዲቋቋም በማድረግ ኢትዮጵያ የፍትሃዊ ተጠቃሚነት መሻቷን በተግባር አሳይታለች ነው ያሉት። ‎ኢትዮጵያ ከጎረቤቶቿ ጋር የህዝብ ለህዝብ ትስስርን ለማጠናከር ለ968 የተለያዩ ሀገራት ዜጎች የትምህርት እድል መስጠቷንም ቃል አቀባዩ ጨምረው ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ ‎የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም የሚያስከብሩ 11 ስምምነቶች ተፈርመው በፓርላማ መፅደቃቸውንም ነው አምባሳደር ነብያት ጌታቸው የገለጹት። በኢኮኖሚ ዲፕሎማሲም ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ስለ ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውና ስለኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ በቂ ግንዛቤ በመያዝ ድጋፉን እንዲያጠናክር የሚያደርጉ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። በበጀት ዓመቱ በዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ በ21 ሀገራት በችግር ውስጥ የነበሩ ከ131ሺህ በላይ ዜጎች ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ መደረጉንም አስታውሰዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበጀት ዓመቱ ‎የዜጎችን ደህንነትና ክብር የማስጠበቅ ሥራን ቀዳሚ ትኩረት ሰጥቶ መስራቱን አመልክተዋል። ‎ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ኮንፍረንሶችን የማስተናገድ አቅሟ እያደገ መምጣቱን የጠቀሱት አምባሳደሩ፣ በቅርቡም ትላልቅ ዓለም አቀፍ ጉባኤዎች ይካሄዳሉ ብለዋል። ከእነዚህም ውስጥ የተባበሩት መንግስታት ሁለተኛው የሥርዓተ ምግብ ጉባኤ እና ሁለተኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባኤ ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአሜሪካ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ከተፈቀደላቸው የቪዛ ጊዜ በላይ መቆየት ከፍተኛ ተጠያቂነትን የሚያስከትል በመሆኑ ዜጎች ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባም ነው ቃል አቀባዩ በመግለጫቸው ያሳሰቡት። የኢትዮጵያን ቪዛ አግኝተው የሚመጡ የሌላ ሀገር ዜጎች ከተፈቀደላቸው የቆይታ ጊዜ በላይ መቆየት በሀገሪቱ ህግ መሰረት ቅጣት የሚያሰጥ መሆኑን በመገንዘብ ጥንቃቄ እንደያደርጉም አፅንኦት ሰጥተዋል።
ምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር ስራን በጥናትና ምርምር በመደገፍ ውጤታማ ተግባር እያከናወነ ነው - አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ
Jul 10, 2025 115
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር ስራን በጥናትና ምርምር በመደገፍ ለአካታች ልማት መሳካት የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን የምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጹ። አፈ ጉባኤው ይህን ያሉት "አካታችና ጠንካራ የፓርላማ ስርዓት ለሀገር በቀል እውቀትና ቀጣይነት ላለው ልማት" በሚል በተጀመረው አምስተኛው ዓመታዊ የፓርላማ ጥናትና ምርምር ኮንፍረንስ መክፈቻ መርሃ ግብር ላይ ነው።   አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ የምርምር ባህልን ማሳደግ ቀጣይነት ላለው እድገት፣ ጠንካራ ምጣኔ ሃብትና ዘላቂ እድገትን ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል። በመሆኑም የምርምር ኮንፍረንሱ ምክር ቤቱ ለሚያወጣቸው ፖሊሲዎች፣ ህጎችና ለሚያደርገው የክትትልና ቁጥጥር ሥራ አስተዋጽኦው ከፍተኛ እንደሆነ አንስተዋል። ምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር፣ የሕዝብ ውክልና እና የፓርላማ ዲፕሎማሲ ሥራዎችን በጥናትና ምርምር የተደገፉ በማድረግ የህዝብን ጥያቄ ለመመለስ እየሰራ ነው ብለዋል። የህዝብ ቅሬታን ከመሰረቱ በጥናትና ምርምር በመለየት በሚወጡ ህጎችና ፖሊሲዎች በማካተት ዘላቂ መፍትሔ እንዲሰጣቸው እያደረገ መሆኑንም ጨምረዋል። ምክር ቤቱ በቀጣይም ከምርምር ተቋማት ጋር ያለውን የትብብር ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።   በአምስተኛው ዓመታዊ የፓርላማ ጥናትና ምርምር ኮንፍረንስ የፓርላማ ዴሞክራሲ ሥርዓት ትግበራ መሻሻል፣ የፓርላማ ተግባራትን ማጠናከር፣ የሕግ የበላይነት፣ አካታች አስተዳደርና ሀገረ መንግሥት ግንባታ ላይ ያተኮሩ 12 የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎች እንደሚቀርቡ የወጣው መርሃ ግብር ያሳያል። በኮንፍረንሱ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከፍተኛ አመራሮች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኃላፊዎች፣ ምሁራንና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።
መንግስት በሁሉም መስክ የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ መሰረት የሚጥሉ ውጤታማ ተግባራትን አከናውኗል
Jul 10, 2025 106
ጎንደር፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፡- በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት መንግስት በሁሉም መስክ የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ መሰረት የሚጥሉ ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑ ተገለጸ። "ጠንካራ አደረጃጀት ለሁለንተናዊ ብልፅግና " በሚል መሪ ሃሳብ የብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ የ2017 በጀት ዓመት ግምገማና የ2018 የእቅድ ትውውቅ መድረክ በጎንደር ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡   በግምገማ መድረኩ ላይ የብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ ሃላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ እንደተናገሩት፤ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት በፓርቲው አመራር ሰጪነት ሀገርን ወደ ብልፅግና የሚያሻግሩና አለም ምስክርነቱን ጭምር የሰጠባቸው ትርጉም ያላቸው ውጤታማ ተግባራት ማከናወን ተችሏል፡፡ የኑሮ ውድነትን በመቀነስ የህዝቡን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል የሚረዱ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርና የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ተጠቃሽ የልማት ተግባራት መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ የከተሞችን እድገት ለማፋጠንና የሕዝቡንም የኑሮ ዘይቤ ለማዘመን እንዲቻል በመላ ሀገሪቱ እየተከናወኑ የሚገኙ የኮሪደር ልማት ስራዎች ከተሜነትን በማላበስ አዲስ ተስፋና ብርሃን የፈነጠቁ ፋና ወጊ የልማት ተግባራት መሆናቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ የዚህ ትውልድ አኩሪ ድልና ታሪክ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብም ስኬት የህዝባችን አይበገሬነትና የፓርቲያችን የአመራር ቁርጠኝነት የታየበት ነው ብለዋል፡፡ የአማራ ክልል እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ባለቤትና በኢትዮጵያ ታሪክም ትልቅ አሻራ ያለው ነው ያሉት አቶ ፍቃዱ፤ የክልሉን ሰላም በማፅናት ልማቱን አጠናክሮ ለማስቀጠል አመራሩና ሕዝቡ ተቀናጅተው ያከናወኑዋቸው ተግባራት የሚደነቁ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ፓርቲው የሚመራው መንግስት በርካታ ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑን ገልጸው፤ ዛሬም እንደ ትናንቱ በሕዝባችን ተሳትፎና በአመራሩ ቁርጠኛ ያልተሻገርናቸውን በድል ለመወጣት መጪው ዓመት በትጋት ለመስራት ቃል የምንገባበት ነው ብለዋል፡፡ በብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ሃላፊ አቶ ፍሰሃ ደሳለኝ በበኩላቸው፤ የአማራ ክልል ትልቅ የመልማትና የማደግ አቅም ያለው የተፈጥሮ ጸጋዎች ባለቤት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የክልሉ ሰላም በማፅናት የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ብልፅግና ፓርቲ የጠራና ተሻጋሪ ሃሳብ ያለው በመሆኑ ሰላምና ልማትን ለማረጋገጥ እየተጋ እንደሚገኝ ገልጸው፤ ፓርቲው ለሕዝቡ የገባውን ቃል አክብሮ ወደ ተግባር በማሸጋገር በኩል ሕዝባዊ አደራውን ይወጣል ብለዋል፡፡ ጎንደር የብልፅግና ትሩፋቶች ተቋዳሽ ከሆኑ የሀገራችን ቀደምት ከተሞች አንዱ ለመሆን በቅታለች ያሉት ደገሞ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ናቸው፡፡   በፌደራልና በክልሉ መንግስት በከተማዋ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች የቀደመ ገናና ስሟንና ታሪኳን ያደሰ ብሎም የኪነ ጥበብና የኪነ ህንጻ አሻራዋን በደማቁ ያጎሉ ተግባራት መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የፓርቲው የአደረጃጀት ዘርፍ የአፈጻጸም ግምገማ መድረክ ላይ ከሁሉም የሀገሪቱ ክልሎች የተውጣጡ የፓርቲው የአደረጃጃት ዘርፍ አመራሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። አመራሮቹ በፌደራልና በክልሉ መንግስት እየተከናወኑ የሚገኙ የሌማት ትሩፋት፣ የኮሪደር ልማት፣ የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት እድሳትና የጥገና ስራ እንዲሁም የመገጭ የመስኖና የመጠጥ ውሃ ግድብ ፕሮጀክቶች ትናንት ተዘዋውረው መጎብኘታቸውን በወቅቱ ተገልጿል።
ኢትዮጵያ በበጀት ዓመቱ ብሔራዊ ጥቅሟን የሚያስጠብቁ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ተግባራትን አከናውናለች - የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
Jul 10, 2025 92
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት ብሔራዊ ጥቅሟን የሚያስጠብቁ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ተግባራት ማከናወኗን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው የበጀት ዓመቱን አበይት የዲፕሎማሲ ክንውኖች አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም በበጀት ዓመቱ በሁሉም የዲፕሎማሲ መስኮች የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም የሚያስጠብቁና የሀገርን ገፅታ የሚያስተዋውቁ የዲፕሎሚሲ ስራዎች መከናወናቸውን አስታውቀዋል። ከጎረቤት ሀገራት ጋር በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ግንኙነትን በኤሌክትሪክ ኃይልና በመንገድ መሰረተ ልማት ይበልጥ የማጠናከርና በአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ስኬታማ ሥራዎች መፈጸማቸውን አብራርተዋል። በበጀት ዓመቱ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን በተመለከተም የኢትዮጵያን እውነታ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ማስረዳት መቻሉን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ ከተለያዩ ሀገራት ጋር በርካታ የሁለትዮሽና የባለብዙ ወገን ስምምነቶች መደረጋቸውንም ነው ያነሱት። እነዚህ ስምምነቶች የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም የሚያስጠብቁና በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተሰሚነትና ተደማጭነት የሚያጎለብቱ ናቸው ብለዋል። በዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲም በተለያዩ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ ኢትዮጵያውያንን ጤንነታቸውና ክብራቸው ተጠብቆ ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ መደረጉን ገልጸዋል።
በሀገሪቱ ስኬቶችን ይበልጥ በማጎልበት የብልፅግና ጉዞውን ለማሳካት የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው ቀጥለዋል
Jul 10, 2025 85
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 3/2017 (ኢዜአ)፡- በሀገሪቱ በተለያዩ ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶችን ይበልጥ በማጎልበት የብልፅግና ጉዞውን ለማሳካት የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸው ተገለጸ። የብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ የ2017 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2018 እቅድ ላይ የሚመክር የጋራ መድረክ በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ነው።   በመድረኩ ላይ የብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ሃላፊ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር) እንዳመለከቱት፤ ፓርቲው በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ባከናወናቸው ተግባራት በርካታ ድሎችና ስኬቶች ተመዝግበዋል። ለተመዘገቡ ድሎችና ስኬቶች በአመራሩ፣ በአባላቱና ሕዝቡ ዘንድ የፓርቲውን አስተሳሰብ በማስረጽ የተከናወኑ ሥራዎች ጉልህ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሁለተኛው ጉባኤ በተሳካ ሁኔታ መከናወኑንም አንስተዋል። በዚህም ጥልቅ ውይይቶችን በማድረግ አመራሩ ፣ አባሉና ሕዝቡ ድሉን እንዲጋራና ለብልጽግና ጉዞ በጋራ እንዲሰራ የሚያደርግ አቅም መፍጠር መቻሉንም ተናግረዋል። በፓርቲው በተቀረጹ የተለያዩ ኢንሼቲቮች የሕብረተሰቡን ህይወት የሚቀይሩ ተግባራት መከናወናቸው ጠቅሰው፤ የብልፅግና ጉዞውን ለማሳካት የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል። ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የተጀመረው ስራ ውጤት እየተመዘገበበት መሆኑን የጠቀሱት ሃላፊው፤ መልካም አስተዳደር ማስፈን፣ የኑሮ ውድነትን ማርገብ፣ ስራ አጥነት መቀነስና መሰረተ ልማት ዘርፎች ላይ የተከናወኑ ሥራዎች የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያግዙ እንደሆኑም አብራርተዋል።   በብልፅግና ፓርቲ የሲዳማ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ አብረሃም ማርሻሎ በበኩላቸው፤ ፓርቲው አዳዲስ ሃሳቦችን በማፍለቅና ወደ ተግባር በመቀየር ያከናወናቸው ተግባራት ተጨባጭ ውጤት ያመጡ ናቸው ብለዋል። የፓርቲው እሳቤዎች፣ የተቀረጹ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች በአመራሩ፣ አባሉና ሕዝቡ ዘንድ ለማስረጽ የፖለቲካና አቅም ግንባታው ዘርፍ በስልጠና የታገዘ ጉልህ ሚና እንዳበረከተም አንሰተዋል። ባለፈው የበጀት ዓመት የተመዘገቡ ስኬቶችን በማስቀጠልና ጉድለቶችን በመለየት ለቀጣይ ጉዞ ውጤታማነት የመድረኩ ሚና ጉልህ መሆኑን ተናግረዋል። ለሶስት ቀናት በሚቆየው መድረክ የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች እየተሳተፉ ሲሆን፤ የመስክ ምልከታም እንደሚካሄድ ይጠበቃል።    
ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያን የግብር ስርዓት በማዘመን የገቢ አሰባሰብ አቅምን ለማሳደግ ያግዛል - ቋሚ ኮሚቴው
Jul 9, 2025 130
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያን የግብር ስርዓት በማዘመን የገቢ አሰባሰብ አቅምን ለማሳደግ የሚያግዝ መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አስታወቀ። ቋሚ ኮሚቴው በፌዴራል የገቢ ግብር አዋጅ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ በዚሁ ወቅት በቋሚ ኮሚቴው አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች የተሰጡት ምላሽና ማብራሪያዎች ግልፅና የተሻለ መረዳት መፍጠር መስቻሉን ተናግረዋል።   ማሻሻያው የግብር አከፋፈል ስርዓትን በማዘመን ግልፅነት በተሞላበትና ፍትሃዊነትን በሚያሰፍን መልኩ ማከናወን የሚያስችል በመሆኑ የሚበረታታ ነው ብለዋል። ማሻሻያው መንግስት ያስቀመጠውን አላማ የሚያሳካና በግብር ከፋዩ ዘንድ የተሻለ መረዳት የሚፈጥር መሆኑንም ጠቅሰዋል። በዚህም ቋሚ ኮሚቴው ለውጤታማነቱ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል።   የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ አብርሃም አለማየሁ(ዶ/ር) በበኩላቸው ረቂቅ አዋጁ በገቢ ዘርፍ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ነው ብለዋል። ዲጂታል ስርዓት ሲዘረጋ ለተገልጋዮች የበለጠ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተው ለዚህም መሰረተ ልማት ከማሟላት አኳያ በቂ ዝግጅት ሊደረግ እንደሚገባ ገልጸዋል።   የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ(ዶ/ር) በሰጡት ማብራሪያ ማሻሻያው የታክስ ህጎች እንዲከበሩ ለማድረግና የመንግስትን ገቢ ለማሳደግ አስፈላጊ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ የረቂቅ አዋጁ ዋነኛ አላማዎች ዝቅተኛ ገቢ ባላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ ያለውን የግብር ጫና መቀነስ፣ የግብር መሰረትን ማስፋት፣ ለአነስተኛ የንግድ እንቅስቃሴዎች ቀላል የግብር አከፋፈል ስርዓት መዘርጋት ናቸው ብለዋል። እንዲሁም ለኢንቨስትመንት የሚደረገውን ጥረት ማገዝ፣ የታክስ ማጭበርበርን መከላከልና ግልጽነት በሚጎድላቸው አንቀጾች ምክንያት የሚደርሱ ውጣ ውረዶችን ለማስቀረት እንደሆነም አክለዋል።
ምርጫ ቦርድ በተለያዩ ጊዜያት ከተካሄዱ ምርጫዎች ተሞክሮ በመውሰድ ማሻሻያዎችን ማቅረቡ ተገቢ ነው - ቋሚ ኮሚቴው
Jul 9, 2025 102
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በተለያዩ ጊዜያት ከተካሄዱ ምርጫዎች ተሞክሮ በመውሰድ ክፍተቶችን መሙላት የሚያስችሉ ማሻሻያዎችን ማቅረቡ ተገቢ መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። ቋሚ ኮሚቴው የኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ስነ-ምግባር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ እውነቴ አለነ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በተለያዩ ወቅቶች ከተካሄዱ ምርጫዎች በመነሳትና የውጪ ተሞክሮን በመቀመር የሀገሪቱን የዲሞክራሲ ስርዓት ለማሳደግ የሚያደርገው ጥረት የሚበረታታ ነው።   ቦርዱ ረቂቅ አዋጁን ሲያዘጋጅ በኢትዮጵያ አካታች የፖለቲካ አካሄድ እንዲኖር ለማድረግ ከፍ ያሉ ስራዎች ማከናወኑን መረዳታቸውን ጠቅሰዋል። በዋናነትም ለወጣቶች፣ ለአካል ጉዳተኞችና ሴቶች አካታች እንዲሆን የሰጠውን ትኩረት አድንቀዋል። በኢትዮጵያ ያለው አዳጊ ዲሞክራሲ በመሆኑ ፓርቲዎች ስህተት በሚፈጥሩበት ጊዜ ማረም ተገቢ መሆኑን ጠቁመው፤ ሕግና ስርዓትን ለማስከበርም በረቂቅ አዋጁ የተካተቱት ጉዳዮች ተገቢ መሆናቸውን ተናግረዋል። የምርጫ አስፈፃሚዎች ቁጥርን አስመልክቶ እንደየስራ ጫናው ሊሆን እንደሚገባ ያመለከቱት የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ከዚህ አኳያ የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ተገቢ እንደሆነ ጠቅሰዋል። ምርጫን በቴክኖሎጂ ለማከናወን በረቂቅ አዋጁ የተቀመጠው ተገቢና አስፈላጊ ከመሆኑ ባለፈ ጊዜውን የዋጀ ነው ብለዋል። ከቅሬታ ሰሚ አኳያም በቀጣይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት የሚደረግበት መሆኑን ነው ሰብሳቢው ያመላከቱት።   የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሮ ሜላትወርቅ ሀይሉ በሰጡት ማብራሪያ፤ ረቂቅ አዋጁ በስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ወቅት በአፈጻጸም ላይ የታዩ ክፍተቶችን መፍታት የሚያስችል ማሻሻያ መደረጉን ገልፀው፤ በዋናነትም የመራጭነትና የዕጩነት ምዝገባና የእድሜ ሁኔታን ያካተቱ አንቀፆች መካተታቸውን ነው የተናገሩት። ረቂቅ አዋጁ በተሻለ መልኩ አካታች የሆነ አካሄድ እንዲከተል የተደረገ ሲሆን፤ ለሴቶችና ለአካል ጉዳተኞችም ልዩ ትኩረት መስጠቱን አስረድተዋል።
በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተገኙ አበረታች ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ - አቶ መለስ አለሙ
Jul 9, 2025 110
ሐረር፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፡- በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተገኙ አበረታች ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በብልፅግና ፓርቲ የዋናው ጽህፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መለስ አለሙ ገለጹ። የፓርቲው የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የ2017 ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2018 እቅድ ተግባቦት መድረክ በሐረር ከተማ መካሄድ ጀምሯል።   አቶ መለስ አለሙ እና በብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ጌቱ ወዬሳን ጨምሮ የፓርቲው የወጣቶችና ሴቶች ክንፍ አመራሮችና ሌሎች የፌደራልና የክልል የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ አመራሮች ተገኝተዋል። በመድረኩ የተገኙት አቶ መለስ አለሙ እንዳሉት በ2017 በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፍ አበረታች ሥራዎች ተከናውነዋል። በበጀት ዓመቱ የተገኙትን ጥንካሬዎች በማስቀጠልና የተስተዋሉ ውስንነቶችን በማረም በ2018 በጀት ዓመት የተሻለ ስራ በማከናወን ለውጡን ማስቀጠል ይገባል ብለዋል። የመሃል ዘመን ፈተናን የምንሻገርበትና አዲስ የማንሰራራት ዘመን መባቻ ላይ የምንገኝ በመሆኑ የ2018 እቅድ ከወትሮው የተለየ ያደርገዋል ነው ያሉት። በተለይ በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራትን በ2018 በጀት ዓመትም በላቀ ደረጃ የምንተገብርበት በመሆኑ ከወዲሁ ዝግጅት እና ልምምድ በማድረግ ወደ ባህል ማሻገር ይገባል ብለዋል። መድረኩም አቅም የምንገነባበትና ትምህርት ወስደን ለቀጣይ በጀት ዓመት ዝግጅት የምናደርግበት ነው ሲሉም ገልጸዋል። መድረኩ በክልሎች መዘጋጀቱ በየአካባቢው ያለውን ባህል ለመረዳት፣ ለመቀራረብና ያሉ ጸጋዎችን ለመረዳት እንዲሁም ተሞክሮ ለመቅሰም እንደሆነም ተናግረዋል።   በብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ጌቱ ወዬሳ በበኩላቸው በክልሉ በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ የተከናወኑ ተግባራት የሴቶችና የወጣቶች ክንፍ እንዲጠናከር እንዲሁም ከሲቪል ማህበራት ጋር ተቀራርቦ የመስራት ተሞክሮን አስፍቷል ብለዋል። በተለይም ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር የነበረውን የተራራቀ አመለካከት በመቅረፍ በልማትና በሰላም ሥራዎች ላይ ተቀራርቦ የመስራት ባህልን አስፍቷል ነው ያሉት። ለሁለት ቀናት በሚቆየው መድረክ የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የ2017 እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት እና የ2018 መነሻ እቅድ ቀርቦ ውይይት ከተካሄደ በኋላ ለቀጣይ አቅጣጫ ይቀመጣል ተብሎ ይጠበቃል። ከመድረኩ ጎን ለጎን በሐረር ከተማ የተከናወኑ የልማት ስራዎች ጉብኝት እና የችግኝ ተከላ መርሀግብር እንደሚከናወን ተመላክቷል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም