ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
በአዲስ አበባ በሚገኘው የስዊዘርላንድ ኤምባሲ ቅጥር ግቢ ውስጥ ሕንጻ ለመገንባት የመሰረት ድንጋይ ተቀመጠ
Mar 19, 2024 73
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 10/2016(ኢዜአ)፦የስዊዘርላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢግናዚዮ ካሲስ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ ጋር በመሆን በአዲስ አበባ በሚገኘው የስዊዘርላንድ ኤምባሲ ቅጥር ግቢ ውስጥ ሕንጻ ለመገንባት የመሰረት ድንጋይ አስቀመጡ። በመርኃ ግብሩ የሁለቱ አገራት የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት የሥራ ኃላፊዎች፣ የስዊዘርላንድ ፓርላማ ተወካዮችና ዲፕሎማቶች ተገኝተዋል። በትላንትናው ዕለት በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት እያደረጉ ያሉት የስዊዘርላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢግናዚዮ ካሲስ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ ጋር በሁለትዮሽ፣ በቀጣናዊና በዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ዙሪያ መወያየታቸው ይታወሳል።
ኢትዮጵያና ግሪክ ለዘመናት የቆየ ግንኙነታቸውን በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በትምህርትና ስልጠናም ያጠናክራሉ - አምባሳደር ደሚቱ ሀምቢሳ
Mar 19, 2024 76
አዲስ አበባ፤መጋቢት 10/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያና ግሪክ ለዘመናት የቆየ ግንኙነታቸውን በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በትምህርትና ስልጠና ማጠናከር እንደሚያስፈልግ አምባሳደር ደሚቱ ሀምቢሳ ገለጹ። ተቀማጭነታቸው በሮም ሆኖ በግሪክ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር ደሚቱ ሀምቢሳ ከግሪክ የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር አምባሳደር አሌክሳንደራ ፓፓዶፖሉ ጋር ተወያይተዋል። በውይይታቸውም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የሁለትዮሽ እና የባለ ብዙ ወገን ግንኙነት የበለጠ ማጠናከር በሚቻልበት ጉዳዮች ዙሪያ መክረዋል። ሁለቱ ሀገሮች ያላቸውን ታሪካዊ ግንኙነት ያወሱት አምባሳደሯ ፣ በሀገራቱ መካከል ያለውን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በትምህርትና ስልጠና ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑንም አንስተዋል። ምክትል ሚኒስትሯ በበኩላቸው ግሪክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ታሪካዊ ግንኙነት ማጠናከር እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል። አክለውም ሀገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር በንግድ፣ በኢንቨስትመንት እንዲሁም በትምህርት ዘርፍ ያላትን ትብብር እንደምታሳድግ መግለጻቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በመዲናዋ በሲቪል ሰርቪስ ተቋማት ላይ ለሚካሄደው የሪፎርም ትግበራ ውጤታማነት አመራሩ በትጋት መስራት ይጠበቅበታል
Mar 18, 2024 275
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ በ16 የሲቪል ሰርቪስ ተቋማት ላይ ለሚካሄደው ሪፎርም ትግበራ ውጤታማነት አመራሩ በትጋት መስራት እንዳለበት የአዲስ አበባ ከተማ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ኃብት ልማት ቢሮ ገለጸ። ቢሮው በ16 ተቋማት ላይ የሪፎርም ስራ የዝግጅት ምዕራፍን በማጠናቀቅ ወደ ትግበራ መሸጋገሩን አስታውቋል፡፡ የቢሮው ኃላፊ ጣሰው ገብሬ(ዶ/ር ) ዛሬ በሰጡት መግለጫ እንደገለፁት በተቋማት የአሰራር ስርዓት ለውጥ በማስፈለጉና ብቃት ያለው የሰው ኃይል አደረጃጀትና ተጠያቂነትን ለማስፈን በ2016 በጀት ዓመት በ16 ተቋማት ላይ የሪፎርም ስራ ሲሰራ ቆይቷል። ሪፎርሙን ተከትሎ የአሰራር ስርዓት ማሻሻያ የማድረግና በሶስተኛ ወገን የሚሰሩ አገልግሎቶችንና ተቋማትን የመለየት ስራ ተከናውኗል ብለዋል። በቴክኖሎጂ የሚደገፉ አገልግሎቶች መለየታቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም የኢንፎርሜሽን ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት መገንባት የሚያስችሉ 42 ፕሮጀክቶች እንደሚተገበሩ አብራርተዋል። የሰራተኛ ብቃት ምዘና በገለልተኛ ተቋማት መሰጠቱንም በመግለጫቸው አንስተዋል። የብቃት ምዘናው ከ19ሺህ በላይ የሆኑ ሰራተኞች መውሰዳቸውን ጠቅሰው ከተፈታኞቹ መካከል 33 ነጥብ 3 በመቶ አመራሮች እንዲሁም 50 ነጥብ 6 በመቶ ሠራተኞች ማለፋቸውን ተናግረዋል። ምዘናውን ካለፉት መካከል 99 በመቶ የሚሆኑ ኃላፊዎች፣ 88 በመቶ የቡድን መሪና ሰራተኞች መመደባቸውን ጠቁመው ፈተናውን ያላለፉትም በድልድል ደንቡ መሰረት ሁለት ደረጃ ዝቅ ብለው መመደባቸውን ገልጸዋል። ምዘናውን ተከትሎ ከ17 ሺህ በላይ ሰራተኞች በሁለት ዙር የአቅም ግንባታ ስልጠና መውሰዳቸውን ተናግረዋል። የሪፎርሙ የዝግጅት ምዕራፍ ተጠናቆ ከዛሬ ጀምሮ ወደ ትግበራ መግባቱን ገልፀው እንደዝግጅት ምዕራፉ ሁሉ ለትግበራ ምዕራፉ ውጤታማነት በተለይ የተቋማት አመራሮች በትጋት መስራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል።
ኢትዮጵያና ስዊዘርላንድ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን በተለያዩ የትብብር መስኮች ለማጠናከር ይሰራሉ
Mar 18, 2024 309
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ለበርካታ ዓመታት የቆየውን ኢትዮጵያንና የስዊዘርላንድ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በተለያዩ የትብብር መስኮች ለማጠናከር በትኩረት እንደሚሰሩ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ በኢትዮጵያ የሥራ ጉብኝት እያደረጉ ካሉት ከስዊዘርላንድ አቻቸው ኢግናዚዮ ካሲስ ጋር በሁለቱ ሀገራት ግንኙነት እንዲሁም በቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ተወያይተዋል። የሀገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ከውይይቱ በኋላ በሰጡት መግለጫ፤ ኢትዮጵያና ስዊዘርላንድ ግንኙነታቸውን በተለያዩ የትብብር መስኮች ለማጠናከር እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ ሁለቱ ሀገራት ረጅም ዓመታትን ያስቆጠረ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያላቸው አገራት ናቸው ብለዋል። በርካታ የስዊዘርላንድ ኩባንያዎች ኢትዮጵያ ውስጥ በኢንቨስትመንት መሰማራታቸውን ጠቁመው ይህንን አጋርነት ይበልጥ ለማጠናከር መግባባት ላይ መደረሱን ገልጸዋል። በሁለቱ ሀገራት መካከል ከዚህ ቀደም የተደረሱ የትብብር ሥምምነቶች ተግባራዊ ለማድረግም እንዲሁ። በሌላ በኩል በፕሪቶሪያው የሠላም ሥምምነት፣ በሽግግር ፍትህና ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የአፈፃጸም ሂደት ላይ አጽንኦት ሰጥተው መምከራቸውንም አንስተዋል። የስዊዘርላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኢግናዚዮ ካሲስ በበኩላቸው፤ የሀገራቱን የሁለትዮሽ ዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነትን አጠናክሮ ለማስቀጠል ተስማምተናል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ልማት፣ ሰላምና ደኅንነት ወሳኝ ሚና የምትጫወት ሀገር መሆኗን ገልጸዋል። ስዊዘርላንድ ከኢትዮጵያ ጋር በንግድ፣ በኢንቨስትመንትና በፍልሰት ጉዳዮች ላይ በትብብር እየሰራች መሆኑን ተናግረዋል። የሥራ ጉብኝታቸውም የስዊዘርላንድና ኢትዮጵያን የቆየ ታሪካዊ ወዳጅነት አጠናክሮ ለማስቀጠል ዓላማ ያደረገ መሆኑንም አንስተዋል።
በሰላም ማስከበር ተልዕኮ ግዳጃቸውን በአኩሪ ገድል በመፈፀም ረገድ የሴቶች ሠራዊት አባላት ሚና እየጨመረ ነው
Mar 18, 2024 213
ድሬዳዋ ፤ መጋቢት 9/2016(ኢዜአ)፦ በተባበሩት መንግስታት የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ግዳጃቸውን በአኩሪ ገድል በመፈፀም ረገድ የሴቶች ሠራዊት አባላት ሚና እየጨመረ መሆኑን ብርጋዴር ጄኔራል ሁሉአገርሽ ድረስ ተናገሩ። ብርጋዴር ጄኔራል ሁሉአገርሽ ይህን የተናገሩት ሁርሶ ኮንቲንጀንት ትምህርት ቤት ለሰላም ማስከበር ተግባር የሰለጠኑ የሠራዊት አባላት ባስመረቀበት ስነስርዓት ላይ ነው። በሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት ብርጋዴር ጄኔራል ሁሉአገርሽ ድረስ በዘመቻው ለሚሳተፉት ተመራቂ ሴት የሠራዊቱ አባላት ተሞክሯቸውን በማካፈል የተሻለ ውጤት እንዲያመጡ አበረታትተዋል። ብርጋዴር ጄኔራል ሁሉአገርሽ በዚሁ ወቅት ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ሴቶች የአገር መከላከያ ሠራዊትን ተቀላቅለው የአገራችንን ዳር ድንበርና ሉዓላዊነት በማስከበር ረገድ እያደረጉት የሚገኘው ተሳትፎና ውጤታማነት እየጨመረ ይገኛል። ከዚህ ጎን ለጎን በተባበሩት መንግስታት የሰላም ማስከበር ተልዕኮ አገራችን ያላትን ከፍታና ተመራጭነት በማሳደግ ረገድም አበርክቷቸው እየጎለበተ መምጣቱን በመግለፅ። ወደ ደቡብ ሱዳን ለሰላም ማስከበር ተልዕኮ የተዘጋጁት ሴት የሠራዊት አባላትና አመራሮች ቁጥር ከምንጊዜውም በላይ ከፍ ማለቱን ለአብነት አንስተዋል። ይህም ሴቶች በአፍሪካ በተለይም በምስራቅ አፍሪካ አገሮችና ህዝቦች መካከል ትስስር በመፍጠርና አስተማማኝ ሰላምና ፀጥታ እንዲሰፍን እየፈፀሙ የሚገኙት ጀብድና ተቀባይነት እያደገ መምጣቱን ያመላክታል ብለዋል። በቀጣይም አገርን በአምባሳደርነት ወክለው ለሰላም ማስከበር በሚጓዙበት አካባቢዎች ህዝባዊ ባህሪያትን በመላበስ አገራዊና ተቋማዊ ግዳጆችን በብቃት በመወጣት የኢትዮጵያን ገፅታ ያሳድጋሉ ብለዋል። ለሰላም ማስከበር ዘመቻ ዝግጁ ከሆኑት የመከላከያ ሠራዊት መካከል ፍሬህይወት ግርማ በሰጠችው አስተያየት እናቶችና አያቶቼ ሴትነታቸው ሳይበግራቸው ለአገር ሉዓላዊነትና ነፃነት የከፈሉትን ዋጋ ተገንዝቤ እኔም ለአገሬ ክብርና ታላቅነት ሠራዊቱን ተቀላቅያለሁ" ብላለች። ይህን የአገር ክብርና ታላቅነት በሰላም ማስከበር ተልዕኮ ላይ በመድገም የሠራዊቱን ህዝባዊነትና ሙያዊ ትህትና ለማረጋገጥ መዘጋጀቷንም ገልጻለች። አገርንና ታላቁን የኢትዮጵያ ሠራዊት በመወከል ለሰላም ማስከበር ተልዕኮ መታጨት በራሱ ሴቶች ያለንን ተሳትፎና ተቀባይነት እያደገ መምጣቱን ያመለክታል ያሉት ደግሞ ሌላዋ የሰላም አስከባሪ መቶ አለቃ ደጅጥኑ አያሌው ናቸው። በምንሰማራበት የሰላም ማስከበር ዘመቻ አኩሪ ገድል በመፈፀም ሠራዊቱ ያለውን ተቀባይነት ይበልጥ እንዲጨምር እተጋለሁ ብለዋል። በተባበሩት መንግስታት የሰላም ማስከበር ተልዕኮ ለማሳካት ወደ ደቡብ ሱዳን ለመጓዝ ከሰለጠኑት መካከል 17 በመቶዎቹ ሴቶች መሆናቸውም በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ ተገልጿል።
በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሩሲያውያን በአዲስ አበባ የሩሲያ ኤምባሲ በተዘጋጀ ድምጽ መስጫ ተገኝተው ድምጽ ሰጡ
Mar 17, 2024 300
የሩሲያ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ድምጽ አሰጣጥ ስነ ስርዓት ከባለፈው አርብ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ቀጥሎ እየተካሄደ እንደሚገኝ ዘገባዎች ያመለክታሉ አዲስ አበባ፣ መጋቢት 8/2016 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሩሲያውያን በአዲስ አበባ የሩሲያ ኤምባሲ በተዘጋጀ ድምጽ መስጫ ተገኝተው በሀገራቸው እየተካሄደ ላለው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ድምጽ ሰጥተዋል። የሩሲያ ማእከላዊ የምርጫ ኮሚሽን በ2024 የሩሲያ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ላይ ከቭላድሚር ፑቲን ጋር የሚፎካከሩ ሶስት እጩዎች መመዝገቡን አስታውቋል። በኢትየጵያ የሩሲያ አምባሳደርን ጨምሮ ሌሎች ሩሲያዊያን በኤምባሲው በተዘጋጀው የድምጽ መስጫ በምርጫው መሳተፋቸውን የኤምባሲው መረጃ ያሳያል፡፡ የሩሲያ ምርጫ ባለፉት ሶስት ቀናት ሲካሄድ የቆየ ሲሆን ዛሬ ማምሻውን የሚጠናቀቅ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በጋምቤላ ክልል ያለውን ሰላም ለማፅናት ለፀጥታ መዋቅር ሪፎርምና አቅም ግንባታ ትኩረት ተሰጥቷል- አቶ ኡሞድ ኡጁሉ
Mar 17, 2024 265
ጋምቤላ ፤ መጋቢት 8 /2016(ኢዜአ)፡-በጋምቤላ ክልል ያለውን ሰላም ለማፅናት ለፀጥታ መዋቅሩ ሪፎርምና አቅም ግንባታ ትኩረት ተሰጥቶ ወደ ተግባር መገባቱን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኡሞድ ኡጁሉ ገለጹ። የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን በቦንጋ የፖሊስ ማሰልጠኛ ተቋም ያሰለጠናቸውን መደበኛ የፖሊስ አባላት ዛሬ አስመርቋል። ርዕሰ መስተዳድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ለክልሉ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች መቃናት ሰላም ወሳኝነት አለው፤ ለሰላም መከበር ደግሞ የፖሊስ አባላት የላቀ ቁርጠኝነት ይጠበቅባቸዋል። አገራዊ ለውጡን ተከትሎ ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው ዘርፎች መካከል የፀጥታ መዋቅር ሪፎርም አንዱ መሆኑን ጠቁመው፤ ይህንኑ መሠረት በማድረግ የክልሉን የፖሊስ አባላት አቅም የመገንባት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በዕለቱ የአቅም ግንባታ ስልጠና ወስደው ያጠናቀቁ የፖሊስ አባላት በቀጣይ የክልሉን ህዝብ ሰላምና ደህንነት በማስጠበቅ ረገድ ኃላፊነታቸውን በቁርጠኝነት ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የክልሉ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ቾል ኩን በበኩላቸው ፤ ክልሉ ሰፊ የድንበር ወሰን የሚጋራ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ ሊከሰቱ የሚችሉ ድንበር ዘለል ወንጀሎችን በመከላከሉ ረገድ ከዕለቱ ሰልጣኝ የፖሊስ አባላት ከፍተኛ ኃላፊነት ይጠበቃል ብለዋል። በተለይም ህገ ወጥ የጦር መሳሪያና ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር እንዲሁም የቀንድ ከብት ዝርፊያ ወንጀሎችን ለመከላከል ለፖሊሶቹ የተሰጠው ስልጠና ትልቅ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል። ተመራቂ የፖሊስ አባላት በክልሉ አልፎ አልፎ የሚስተዋሉ የፀጥታ ችግሮችን ለመከላከል የሚያስችል አቅም የገነቡ መሆናቸውን የገለፁት ደግሞ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ኡሞድ ኡሞድ ናቸው። በተለይም በከተማ ውስጥ የሚከሰቱ የስርቆትና ሌላው የወንጀል ድርጊት በመከላከል ረገድ የዛሬው ተመራቂ የፖሊስ አባላት በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በአማራና ትግራይ ክልሎች መካከል የሚገኙና የወሰን ይገባኛል ጥያቄ የሚነሳባቸውን አካባቢዎች በህገ መንግስቱ እና በህገ መንግስታዊ ስርዓቱ መሰረት በዘላቂነት እልባት ለመስጠት በብሔራዊ ደረጃ የተቋቋመው ኮሚቴ አፈጻጸም ተገመገመ
Mar 16, 2024 576
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ በአማራና ትግራይ ክልሎች መካከል የሚገኙና የወሰን ይገባኛል ጥያቄ የሚነሳባቸውን አካባቢዎች በህገ መንግስቱ እና በህገ መንግስታዊ ስርዓቱ መሰረት በዘላቂነት እልባት ለመስጠት በብሔራዊ ደረጃ የተቋቋመው ኮሚቴ አፈጻጸም ተገምግሟል። በአማራና ትግራይ ክልሎች መካከል የሚገኙና የወሰን ይገባኛል ጥያቄ የሚነሳባቸውን አካባቢዎች በህገ መንግስቱ እና በህገ መንግስታዊ ስርዓቱ መሰረት በዘላቂነት እልባት ለመስጠት በብሔራዊ ደረጃ ኮሚቴ ተቋቁሞ ሲሠራ ቆይቷል። ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር አቶ ተመስገን ጥሩነህ፣ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን እና የሁለቱ ክልሎች ርዕሳነ መስተዳድሮች እንዲሁም ጉዳዩ የሚመለከታቸው ተሳታፊዎች በተገኙበት የብሔራዊ ኮሚቴው አፈፃፀም ተገምግሟል። የተፈፀሙና ሊፈፀሙ ሲገባቸው የዘገዩ ጉዳዮች ተነስተው ግምገማ ተደርጎባቸዋል። በግምገማው መሰረት በአፈፃፀም ሂደቱ የነበሩ ጠንካራና ደካማ ጎኖች የተለዩ ሲሆን የማንነትና የይገባኛል ጥያቄ ያለባቸውን አካባቢዎች ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች በአፋጣኝና በዘላቂነት ሊፈታ እንደሚገባም ስምምነት ላይ ተደርሷል። ከዚህ አኳያ ተፈናቃዮችን በአጭር ጊዜ ወደቀያቸው የመመለስ ጉዳይ ቅድሚያ ተሰጥቶት በሚፈፀምበት አግባብ ላይ መተማመን ላይ መደረሱም ተጠቁሟል። በተጨማሪም በብሔራዊ ደረጃ ይህን እንዲያስፈፅም የተቋቋመው ኮሚቴ በቋሚ የጊዜ ሰሌዳ እየተገናኘ በአጭር ጊዜ ውስጥ ለጉዳዩ እልባት እንዲሰጥ በዛሬው ዕለት በተደረገው ስብሰባ መወሰኑን ከብሔራዊ ኮሚቴው የደረሰን መረጃ ያመለክታል።
በክልሉ ሠላምና ፀጥታን ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ባሉ ሥራዎች ውጤት ተገኝቷል- አቶ አህመድ ሽዴ
Mar 16, 2024 399
ሀዋሳ ፤መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል ሠላምና ፀጥታን ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ባሉ ሥራዎች ውጤት መመዝገቡን የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ ገለጹ። በሚኒስትሩ የተመራ የፌዴራል የክትትልና ድጋፍ ቡድን በሲዳማ ክልል በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት በተከናወኑ የልማት ሥራዎች ላይ ከክልሉ የሥራ ሃላፊዎች ጋር ዛሬ ተወያይቷል። ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ በመድረኩ እንደገለጹት፣ በክልሉ የህብረተሰቡን ሰላምና ጸጥታ ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ባሉ ሥራዎች አበረታች ውጤት ተመዝግቧል። የፀጥታ አካሉ የጸጥታ ሥራውን በቴክኖሎጂ በማስደገፍና በህዝብ ተሳትፎ ውጤት መመዝገቡን ገልጸው፣ በክልሉ ሕግ የማስከበር አቅምና ብቃት እያደገ መምጣቱንም ተናግረዋል። የሲዳማ ክልል ከአጎራባች ክልሎች ጋር ያለው ሠላማዊ ግንኙነት ተጠናክሮ እንዲቀጥል የተጀመሩ ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚገባም አስገንዝበዋል። በክልሉ ህብረብሔራዊ አንድነትን በማጠናከር በከተሞችና በገጠር የሚኖሩ ዜጎች በሠላምና በነፃነት እንዲኖሩ የተሰሩ ሥራዎች ውጤታማ በመሆናቸው ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ሲሉም ሚኒስትሩ ተናግረዋል። ክልሉ ኢትዮጵያን ከጎረቤት ሀገራት የሚያገናኝ ዋና መንገድ አቋርጦት የሚያልፍ ከመሆኑና ካለው የኮሪደርነት ሚና አኳያ ከፍተኛ የኮንትሮባንድ እንቅስቃሴ እንደሚስተዋልበት አንስተው፣ ኮንትሮባንድን ለመከላከል የተጠናና ቅንጅታዊ አሰራር ማጎልበት ይገባል ሲሉ አሳስበዋል። የሲዳማ ክልል ሠላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ አለማየሁ ጢሞቲዎስ በበኩላቸው እንደተናገሩት፣ የክልሉን ሰላም ዘላቂና አስተማማኝ ለማድረግ ህብረተሰቡን ያሳተፉ ሥራዎች እየተሰሩ ነው። ከእነዚህ ሥራዎች መካከልም በህብረተሰቡ ተሳትፎ የተገነቡ የፖሊስ ተቋማት በቀዳሚነት ይጠቀሳሉ ብለዋል። አቶ አለማየሁ እንዳሉት በ90 ቀናት ውስጥ በ580 ቀበሌዎች እያንዳንዳቸው ከ300 ሺህ ብር እስከ 1 ነጥብ 1 ሚሊዮን ብር ወጪ የተደረገባቸው የፖሊስ መረጃ መቀበያና ማረፊያ ማዕከላት ተገንብተው ለአገልግሎት በቅተዋል። በክልሉ በአጠቃላይ 44 የወረዳ እና የከተማ መዋቅሮች እንዳሉ የጠቆሙት አቶ አለማየሁ፣ "ከነዚህ ውስጥ በራሳቸው ሕንፃ የፀጥታ አካላት ጽህፈት ቤት ያላቸው መዋቅሮች 14ት ብቻ ናቸው" ብለዋል። በዚህም በክልል ደረጃ በየወሩ ከ15 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ለጸጥታ አካላት ጽህፈት ቤት ኪራይ ይወጣ እንደነበር አስረድተዋል። "ለ30 የወረዳ መዋቅሮች ጽህፈት ቤት ለመገንባት መንግስትን ከፍተኛ መዋዕለንዋይ ይጠይቃል" ያሉት አቶ አለማየሁ፣"በአሁን ወቅት በህብረተሰብ ተሳትፎ በሁሉም መዋቅሮች የጽህፈት ቤት ግንባታ እየተካሄደ ይገኛል" ብለዋል። እያንዳንዳቸው ከ25 ሚሊዮን እስከ 40 ሚሊዮን ብር በጀት እየተገነቡ መሆኑንና ከእነዚህ ውስጥ የ20ዎቹ ግንባታ በአሁኑ ወቅት መጠናቀቁንና በቅርቡ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚሆኑ አስታውቀዋል። በሀዋሳ ከተማ በተለያዩ አቅጣጫዎች ዘመናዊ የደህንነት ካሜራዎችን በመጠቀም የተጠናከረ የጸጥታ ሥራ እየተከናወነ መሆኑንም አቶ አለማየሁ ተናግረዋል። እንዲሁም በከተማዋ የሚገኙ 590 የግል ተቋማት ከፀጥታ መዋቅሩ ጋር በመናበብ የራሳቸው የደህንነት ካሜራ እንዲገጥሙ ተደርጓል ብለዋል። የሀዋሳ ከተማ ፖሊስ መምሪያ አዛዥ ምክትል ኢንስፔክተር መልካሙ አየለ በበኩላቸው በከተማዋ ህብረተሰብን በማሳተፍ በተደጋጋሚ ወንጀል የሚፈጸምባቸው አካባቢዎችን በመለየት 40 የፖሊስ መረጃ መቀበያና ማረፊያ ማዕከላት መገንባታቸውን ተናግረዋል። ማዕከላቱ ህብረተሰቡ ከወትሮው በበለጠ ከፖሊስ ጋር ተቀራርቦ እንዲሰራ ምቹ ሁኔታን መፍጠራቸውን ገልጸው፣ ህብረተሰቡና የጸጥታ ሀይሉ ባደረገው ቅንጅት በከተማዋ አስተማማኝ ሰላም ሰፍኗል ብለዋል። መድረኩ በሌሎች ሴክተር ተቋማት የሥራ ክንውን ላይም መምከሩን የቀጠለ ሲሆን በክልሉ በስድስት ወራት ውስጥ የተከናወኑ ዋና ዋና የልማት ሥራዎች ላይ ያተኮረ የመስክ ምልከታም እንደሚደረግ ታውቋል።
የትምህርት ተቋማት በፌዴራሊዝም ስርዓትና ህገ መንግስት ዙሪያ ግንዛቤ የሚያሳድጉ ስራዎችን እንዲያጠናክሩ ተጠየቀ
Mar 16, 2024 336
አዳማ ፤መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦የትምህርት ተቋማት በፌዴራሊዝም ስርዓትና ህገ መንግስት ዙሪያ የህብረተሰቡን ግንዛቤ የሚያሳድጉ ስራዎች እንዲያጠናክሩ ተጠየቀ። የፌዴሬሽን ምክር ቤት ከህገ መንግስትና የፌዴራሊዝም አስተምህሮ ማዕከል ጋር በመተባበር ''ህብረ ብሔራዊ ፌዴራሊዝም፣ የዴሞክራሲያዊ ስርዓት እና የሀገረ መንግስት ግንባታ ዙሪያ የትምህርት ተቋማት ሚና'' በሚል ርእስ በአዳማ ከተማ ምክክር አካሄዷል፡፡ በዚሁ ወቅት የህገ መንግስትና ፌዴራሊዝም አስተምሮ ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሀይለየሱስ ታዬ፣ የምክክር መድረኩ ዓላማ በእኩልነት ላይ የተመሰረተ የፌዴራሊዝም ስርዓትን ለማጎልበት ነው ብለዋል። ይህም በመሆኑ ዜጎች ሀገሪቱ በምትመራበት ህግና ስርዓት ላይ በቂ ግንዛቤና እውቀት እንዲኖራቸው ማድረግ አስፈላጊ ነው ሲሉም ገልጸዋል። በሀገሪቱ የፌዴራሊዝም ስርዓትን ማስገንዘብ ከፍተኛ ኃላፊነት ከተጣለባቸው አካላት መካከል የትምህርት ተቋማት ቀዳሚ መሆናቸውን ጠቅሰው ተቋማቱ በዚህ ዙሪያ የህብረተሰቡን ግንዛቤ የሚያሳድጉ ስራዎች እንዲሰሩ ጠይቀዋል። በትምህርት ተቋማት የሚያልፉ ዜጎች በቂ የሆነ የመንግስት አስተዳደር ስርዓትን በአግባቡ እንዲገነዘቡ የጀመሩትን ስራ ማጠናከር እንዳለባቸውም አመልክተዋል። በፌዴሬሽን ምክር ቤት የመንግስት ግንኙነት፣ ብዝሃነትና የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዳይሬክተር አቶ ትግሉ መለሰ በበኩላቸው የፌዴራሊዝም ስርዓትን ለዜጎች ማስገንዘብ ጠንካራ ሀገራዊ አንድነት እንዲኖር ያስችላል ብለዋል። ትውልዱ መማር ያለበት አንድነትና አብሮነትን ነው ያሉት አቶ ትግሉ ከዚህ አኳያ የትምህርት ተቋማት ሚናቸው ከፍ ያለ መሆኑን ገልጸዋል። ተማሪዎች ለሀገር የሚያስቡና መልካም ስነ-ምግባር የተላበሱ እንዲሁም በእውቀትና ክህሎትም የበለጸጉ እንዲሆኑ ሁሉም ድርሻውን ሊወጣ ይገባልም ብለዋል። በትምህርት ሚኒስቴር ስርዓተ ትምህርት ዴስክ ኃላፊ የሆኑት አቶ ኡመር ኢማም፣ በሀገሪቷ የተሻለ የዴሞክራሲ ስርዓት ለመገንባት የትምህርት ተቋማት ትልቅ ሚና እንዳላቸው ገልፀዋል። የዴሞክራሲ ስርዓትን አስፈላጊነት ለትውልዱ በማሳወቅ ረገድ የትምህርት ተቋማት ድርሻቸውን መወጣት እንዲችሉ አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።
ኮሪያ ሪፐብሊክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከርና ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ ቁርጠኛ ነች
Mar 16, 2024 275
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 7/2016(ኢዜአ)፦ ኮሪያ ሪፐብሊክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት የበለጠ ለማጠናከርና ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ ቁርጠኛ መሆኗን በኢትዮጵያ የኮሪያ ሪፐብሊክ አምባሳደር ጁንግ ካንግ ገለፁ። አምባሳደር ጁንግ ካንግ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ኮሪያ ሪፐብሊክና ኢትዮጵያ ጠንካራና ረዥም ዘመን ያስቆጠረ ታሪካዊ ወዳጅነት ያላቸው ሀገራት ናቸው። ሀገራቱ ግንኙነታቸውን የጀመሩት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1950ዎቹ የኢትዮጵያ ወታደሮች ለኮሪያ ነፃነት በጀግንነት ከተዋጉበት ጊዜ ጀምሮ እንደሆነ አንስተዋል። ይህም ለሁለቱ ሀገራት ወዳጅነትና ትብብር ጠንካራ መሠረት መሆኑን ገልፀዋል። ባለፉት ዓመታት ሀገራቱ በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በልማት ትብብርና ባህል ልውውጥን ጨምሮ በተለያዩ መስኮች ግንኙነታቸውን አጠናክረው መቀጠላቸውን አመላክተዋል። በቀጣይም የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት የበለጠ ለማጎልበትና አጋርነቱን ወደ ላቀ ደረጃ ለማድረስ ሀገራቸው ቁርጠኛ መሆኗን ነው አምባሳደሩ ያረጋገጡት። በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የመካከለኛው ምስራቅ፣ ኤዥያና የፓስፊክ ሀገራት ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር ገበየሁ ጋንጋ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያና ኮሪያ ሪፐብሊክ ከዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ባሻገር ጠንካራ የሕዝብ ለሕዝብ ትስስር አላቸው። ሁለቱም ሀገራት አሁን ላይ ግንኙነታቸው እያደገ መምጣቱን፣ በንግድና ኢንቨስትመንት እንዲሁም በቴክኖሎጂ መስኮች በጋራ መሥራታቸውን ጠቅሰው፤ የልማት ትብብሩም እየተጠናከረ መምጣቱን አስረድተዋል። የኢትዮጵያና የኮሪያ ሪፐብሊክ ይፋዊ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1963 መጀመሩን መረጃዎች ያመላክታሉ።
ኢኮኖሚያዊ ና ማህበራዊ ጥቅሞችን ለመመለስ ህዝባዊ የውይይት መድረኮች ወሳኝ ሚና ይጫወታሉ- ዶክተር ለገሰ ቱሉ
Mar 16, 2024 216
አዲስ አበባ ፤መጋቢት 7/2016( ኢዜአ)፦ኢኮኖሚያዊ ና ማህበራዊ ጥቅሞችን ለመመለስ ህዝባዊ የውይይት መድረኮች ወሳኝ ሚና እንደሚጫወቱ የመንግስት ኮሚኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዶክተር ለገሰ ቱሉ ገለጹ ። ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ ህዝባዊ የውይይት መድረኮች ዜጎች የሀገራቸውን መሰረታዊ የችግር መንስኤዎች እና መፍትሔዎች ዙሪያ ግንዛቤ እንደሚያሳድጉ ገልጸዋል። የተለያዩ ወገኖች ሃሳባቸውን በነፃነት እንዲገልጹ እና ድምጻቸውን ለማሰማት እንደሚያስችላቸውም አመልክተዋል። ውይይቶቹ በመረጃ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ ለመስጠት፣ የተለያዩ ፍላጎቶችን ለማጣጣም እና ለግጭት አፈታት አስተዋፅኦ ማድረግ ይችላሉም ብለዋል። እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ ህዝባዊ ውይይቶች እንደ የደህንነት ቫልቭ ሆኖ የሚያገለግሉ ናቸዉ፡፡ ይህም የተለያዩ ማህበረሰቦች በውስጣቸው ያለዉን ውጥረት እንዲያረግቡ፣ የጋራ መግባባት እንዲፈጥሩ እና በሰላም አብሮ ለመኖር እንዲሰሩ ያስችላቸዋል ። ባላፉት ሳምንታት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሀገሪቱ ከሚገኙ ክልሎች ከተዉጣጡ የማህበረሰብ ክፍሎች ጋር ያካሄዷቸው እና የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች በሀገሪቱ በሚገኙ ዋና ዋና ከተሞች፣ ያደረጓቸው ውይይቶች ከላይ የተጠቀሱ መሰረታዊ መርሆዎችን ለማሳካት ያለሙ ናቸው ብለዋል። ህዝባዊ የውይይት መድረኮቹ በሁለቱ ከተማ አስተዳዳሮች እና በክልሎች ከ70 ባለነሱ ዋናዋና ከተሞች መካሄዳቸውን አንስተዋል። በውይይቱ ህዝቡ ከመንግስት ጋር በጋራ ጉዳዮች ለመወያየት ፍላጎትና ቁርጠኝነቱን ያሳየበት ነው ሲሉ መሪዎቹንም ያበረታታበት፣ ጉድለቶችንም መንግስት እንዲያርም በነፃነት የገለጸበት ነው ብለዋል፡፡ ጥያቄዎቹንም ሚዛናዊና ምክንያታዊ በሆነ መልኩ ያነሳበት፣ የተሰሩ ስራዎችን እውቅና የሰጠበትና ቀጣይነት እንዲኖራቸው የጠቆመበት መሆኑን አንስተዋል። የተጀመሩ የለውጥ ስራዎች ይበልጥ እንዲጠናከሩ ፍላጎቱን የገለፀበት፣ ህዝቡ ለሰላሙም ሆነ ለልማቱ ከፍተኛውን ድርሻ በመወጣት የወረስነውን እዳ ወደ ምንዳ ለመቀየር በከፍተኛ ተነሳሽነት እና በቁጭት ለመስራት፣ ሀብት ለመፍጠር እና የወል ትርክት ላይ በማተኮር ህብረብሄራዊ አንድነትን ለማረጋገጥ ዝግጁነቱን ያረጋገጠበት ነዉ ብለዋል ሚኒስትሩ፡፡ ከፍተኛ አመራሩም የህዝቡን የማልማት ፍላጎቶች እና እንዲቀረፉ የሚፈልጋቸዉን መሰረታዊ ጉዳዮች ለመረዳት ብሎም አንዱ የሌላውን አካባቢ ችግሮች መገንዘብ እንዲችል እድል ያገኘበት እንደነበረም ገልጸዋል፡፡ ከሰላምና መረጋጋት፣ ከኑሮ ውድነት የስራ እድል ፈጠራ፣ የመሰረተ ልማቶች አቅርቦቶች በተለይም የንጹህ መጠጥ ውሃ፣ የኤሌክትሪክ ፣ መንገድ ፣ ቴሌኮም አገልግሎት አቅርቦት እና ሌሎች የልማት ስራዎች በስፋት የተነሳበትና በችግሮች አፈታት ላይ የጋራ መግባባት የተፈጠረበት መሆኑንም አብራርተዋል፡፡ እንደ ዶክተር ለገሰ ገለጻ ከልማት አኳያ የተነሱ ጉዳዮች በጥቅሉ በሶስት ተከፍሎ ሊታዩ የሚችሉ ናቸው። በዕቅድ የተያዙ፣ በቂ በጀትም የተመደበላቸዉ እና በአስተዳደራዊ ችግሮች ምክንያት በወጉ ያልተፈጸሙ ስራዎች መኖራቸውን አንስተው የነዚህን መሠረታዊ ችግሮች ለይቶ በፍጥነት መፍታት ይገባል ብለዋል፡፡ በዕቅድ የተያዙ ነገር ግን በበጀት እጥረት ምክንያት ያልተፈፀሙትን ህብረተሰቡን በማስተባበር፣ ከአጋር አካላት ሀብት በማፈላለግ እና ልዩ ልዩ የፈጠራ መንገዶችን በመጠቀም መፍታት እንደሚገባ አመልክተዋል፡፡ በእቅድ ያልተያዙ፣ ሰፊ ሀብት እና ጊዜ የሚጠይቁትን ከማልማት እና በፍጥነት ለመበልጸግ ከመፈለግ ጋር የተነሱ ጉዳዮች ደግሞ በመካከለኛ እና ረጅም ጊዜ እቅድ ውስጥ በማካተት በቅደም ተከተል መፍታትን ይጠይቃል ነው ያሉት፡፡ እንዲህ አይነቶቹ መድረኮች በቀጣይም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳላባቸዉ ዶክተር ለገሰ ገልጸዋል። በቅርቡ በተካሄደዉ የሚንስትሮች ምክር ቤት የመቶ ቀናት የእቅድ አፈጻጸም ግምገማ እነዚህ ጉዳዮች ተነስተዉ ከላይ በተቀመጠዉ አግባብ እንዲፈቱና የሚመለከታቸው ተቋማት በአጭር፣ መካከለኛ እና ረጅም ጊዜ እቅዳቸዉ እንዲያከትቱ አቅጣጫ መቀመጡን ጠቁመዋል፡፡
የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን የአጀንዳ አሰባሰብ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ላይ ውይይት እያካሄደ ነው
Mar 16, 2024 210
አዲስ አበባ ፤ መጋቢት 7 /2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በአጀንዳ አሰባሰብ ማስጀመሪያ መርሃ-ግብር ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት እያካሄደ ነው። በዚሁ ውይይት ማስጀመሪያ ላይ ንግግር ያደረጉት የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርዓያ፤ ኮሚሽኑ መግባባት ላይ ባልተዳረሰባቸው ጉዳዮች መግባባት ላይ እንዲደረስ እየሰራ ይገኛል። በዚህም ኢትዮጵያውያን ተወያይተው የጋራ መፍትሔ እንዲያስቀምጡ እየተሰራ መሆኑን አስታውቀዋል። ኮሚሽኑ በወረዳዎች ደረጃ ሲያከናውን የቆየውን የተሳታፊ ልየታ ሥራዎች በተሳካ ሁኔታ ማካሄዱን ገልፀዋል። ሀገራዊ ምክክር ለሀገረ- መንግሥት ግንባታ ታላቅ መሠረት የሚጥል ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፤ አሁን ላይ ወደ ተግባር ምዕራፍ እየገባ መሆኑንም ተናግረዋል። ኮሚሽኑ ከዚህ ቀደም ለምክክሩ ወሳኝ እና ተከታታይ የሆኑ ሥራዎችን ሲሰራ መቆየቱን ገልጸው፤ ለዚህም በርካታ ተባባሪ አካላት መሳተፋቸውን ተናግረዋል። ለበርካታ የማኅበረሰብ ክፍሎች በሀገራዊ ምክክር ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ መሰጠታቸውንም ገልፀዋል። በሀገራዊ የምክክር ሂደት ለትውልድ የምትመች ሀገር ለማስተላለፍ እንደሚረዳ ጠቁመዋል። በዛሬው ዕለትም የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን የአጀንዳ አሰባሰብ ሂደት ማስጀመሪያ የአሰራር ስርዓት ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት እያካሄደ ነው ብለዋል። እየተካሄደ በሚገኘው የውይይት መድረክ ሚኒስትሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች፣ ከሁሉም ክልሎች የተወከሉ ባለድርሻ አካላት፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ተወካዮች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
ለሰላምና አንድነት የሚተጋ ማህበረሰብ በመገንባት የድርሻችንን እንወጣለን - አባገዳና ሀደሲንቄ
Mar 16, 2024 181
አዳማ፤ መጋቢት 7/2016 (ኢዜአ)፦ ለሰላምና አንድነት የሚተጋ ማህበረሰብ በመገንባት የሚጠበቅባቸውን ድርሻ እንደሚወጡ ኢዜአ ያነጋገራቸው የምሥራቅ ሸዋ ዞን አባገዳና ሀደሲንቄ ተናገሩ። በአዳማ ከተማ አስተዳደር ባህልና ቱሪዝም ጽህፈት ቤት አዘጋጅነት ባህላዊ ፍርድ ቤቶች በግጭትና አለመግባባቶች አፈታት ላይ እያመጡ ያለውን ለውጥ በተመለከተ ሰሞኑን ውይይት ተካሄዷል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የምስራቅ ሸዋ ዞንና አዳማ ከተማ አባገዳዎች ሰብሳቢ አባገዳ ረታ ያኢቦሩ፣ ለሰላምና አንድነትን ቅድሚያ የሚሰጥ ማህበረሰብ በመገንባት የሀገር ሰላም እንዲጠበቅ ድርሻችንን በመወጣት ላይ ነን ብለዋል፡፡ አባገዳዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና ሀደሲንቄዎች የሀገር ሰላምን በማስጠበቅ በኩል ሊኖራቸው የሚገባው ትልቁ ድርሻ በየአካባቢያቸው ግጭቶችን ከምንጫቸው በማጥራትና ለማህበረሰቡ ቅርብ መሆን ነው ሲሉም አክለዋል፡፡ አባገዳዎችና ሀደሲንቄዎች በጋራ በመሆን በባህላዊ ፍርድ ቤቶች በርካታ አለመግባባቶችን በእርቅ በመፍታት ሰላም እንዲሰፍን ጥረት ከማድረግ ባሻገር፤ ማህበራዊ ግንኙነቶች እንዳይሻክሩ ወግና ስርዓት እንዲጠናከር ማድረግም ይገባል ነው ያሉት፡፡ በተለይ ወጣቶች ከግጭት ይልቅ ጉልበታቸው ለሀገር ልማት እንዲያውሉ በመምከር፣ የጋራ መግባባት እንዲፈጥሩ በማወያየትና ምክር በመስጠት ሚናቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል፡፡ ሀደሲንቄ ፍቅሬ ጫጫ፣ በአካባቢያቸው በወጣቶች ወይም በሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች መካከል የሚፈጠሩ አለመግባባቶችን በመፍታት ሰላም እንዲሰፍን እያደረጉ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአካባቢያቸው ልማድ አንዲት ሴት ሲንቄዋን ይዛ ጠብ ባለበት መሃል ከቆመች ግጭቱን የማስቆም አቅም ያላት በመሆኑ እንደሰላም ተምሳሌት ትቆጠራለች ሲሉም ያስረዳሉ ፡፡ ይህን ባህላዊ ሰላም የሚያሰፍኑ እሴቶቻንን በማስጠበቅም ትውልዱ ችግሩን በመመካከር እንዲፈታ በማድረግ ሚናቸውን እየተወጡ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ችግሮችን በውይይትና በመግባባት ለመፍታት ጥረት ማድረግና ሀገራዊ አንድነትን እንዲፈጥሩ የበኩላችንን እየተወጣን እንገኛለን ብለዋል፡፡ የአካባቢያችንን ሰላም ስናስጠብቅ ሀገራችን ሰላሟ ይረጋገጣል ያሉት ሀደሲንቄ ፍቅሬ፣ ሰላምን ለማረጋገጥ መስራት ይጠበቅብናል ሲሉም አክለዋል።
ከንቲባ አዳነች የአፍሪካ የዓመቱ ምርጥ መሪ ሽልማትን አሸናፊ ሆኑ
Mar 15, 2024 589
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2016(ኢዜአ)፦ ከንቲባ አዳነች አቤቤ መቀመጫውን በእንግሊዝ ያደረገዉ እና በየዓመቱ በአፍሪካ ምርጥ ብቃት ያሳዩ አፍሪካውያን መሪዎችን የሚሸልመው የአፍሪካ ሊደርሺፕ መጽሄት የሚያዘጋጀው የአፍሪካ የዓመቱ ምርጥ መሪ(African leadership magazine person of the year) ሽልማትን አሸናፊ ሆነዋል:: ከንቲባ አዳነች ሽልማቱን ያሸነፉት የመጀመሪያ የአዲስ አበባ ሴት ከንቲባ መሆናቸው ከከንቲባ ጽሕፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል። ሙስናን በመዋጋት ፣ ተቋማዊ ሪፎርሞችን በመተግበር ፣ መልካም አስተዳደር በማስፈን ፣ በአመራር ብስለት እንዲሁም ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ስራዎች ላይ ባሳዩት ውጤታማ ስራ መሆኑም በመድረኩ ላይ ተገልጿል:: ከቀድሞ የታንዛኒያ ፕሬዝዳንት ዶክተር ጃካያ ኪኪዌቴ እጅ ሽልማቱን የተቀበሉት ከንቲባ አዳነች አቤቤ ስለተበረከተላቸው ሽልማት ምስጋናቸውን አቅርበዋል:: “የማይበገር የአፍሪካ ኢኮኖሚ መገንባት” በሚል መሪ ቃል በተካሄደዉ የሽልማት መርሃ ግብር ላይ ዘጠኝ ተጽዕኖ ፈጣሪ አፍሪካዊያን መሪዎች ተሸላሚ መሆናቸው ተገልጿል።
የአማራ ክልልን ወደ ዘላቂ ሰላምና ልማት ለማሸጋገር ተቋማት የድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል- አቶ ደሳለኝ ጣሰው
Mar 15, 2024 298
ባህር ዳር ፤ መጋቢት 6/2016(ኢዜአ)፡- የአማራ ክልልን ወደ ዘላቂ ሰላምና ልማት ለማሸጋገር የአስተዳደር ዘርፍ ተቋማት የድርሻቸውን መወጣት እንዳለባቸው በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የአስተዳደር ዘርፍ አስተባባሪና የክልሉ የሰላምና ፀጥታ ቢሮ ሀላፊ አቶ ደሳለኝ ጣሰው አሳሰቡ። የሰላም እና ጸጥታ፣ ሚሊሻ፣ ፖሊስ፣ ፍትሕ፣ ርዕሰ መስተዳድር ጽሕፈት ቤት፣ ሲቪል ሰርቪስ፣ ፀረ ሙስና ኮሚሽን እና በየደረጃው የሚገኙ ተቋማት የሥራ ኀላፊዎች ሰባት ወራት የስራ አፈጻጸም ዛሬ ገምግመዋል። የቢሮ ሃላፊው አቶ ደሳለኝ ጣሰው እንደገለጹት፤ የአስተዳደር ዘርፍ ተቋማት ለሰላም መስፈን ዓይነተኛ ሚና ይጫወታሉ። ህብረተሰቡ የሚፈልጋቸው የመልካም አስተዳደርና የፍትህ አገልግሎቶችን ተቋማቱ ግልጽነትና ፍትሃዊነትን በማስፈን መልካም አስተዳደርን ማረጋገጥ እንደሚጠበቅባቸው ተናግረዋል። በዚህ መድረክ ችግሮቻቸውን በመለየትና የመፍትሄ አቅጣጫ በማመላከት የመልካም አስተዳደር የሰፈነበት አገልግሎት በመስጠት ለክልሉ ሰላም መስፈን የአንበሳውን ድርሻ ሊወጡ እንደሚገባ አሳስበዋል። ለዚህ ደግሞ እያንዳንዱ የአስተዳደር ተቋማት የሰው ሀብታቸውን የማብቃትና ቁርጠኝነትን በማሳደግ መንግስትና ህዝብ የሚፈልጉትን ለውጥ ማረጋገጥ እንዳለባቸው አሳስበዋል። በግምገማ መድረኩ የክልሉ የድርጅት፣ የሰላምና ፀጥታ የዞን አስተዳዳሪዎች፣ የክልሉ የፖሊስ ኮሚሽን፣ ፍትህ ቢሮ አመራር አባላትና ሌሎች ባለ ድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
የሕገ-መንግሥት አጣሪ ጉባኤ ያዘጋጀው የአሰራር ሥነ-ሥርዓት ደንብ ለተቀላጠፈ አገልግሎት ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ
Mar 15, 2024 263
አዲስ አበባ፤መጋቢት 6/2016(ኢዜአ)፦የሕገ-መንግሥት አጣሪ ጉባኤ የአሰራር ሥነ-ሥርዓት ረቂቅ ደንብ ጸድቆ ወደ ሥራ ሲገባ ዜጎች ለሚነሷቸው የሕገ-መንግሥት ትርጉም ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ ለመስጠት እንደሚያስችል ተመላከተ። የሕገ-መንግሥት ጉዳዮች አጣሪ ጉባዔ የአሰራር ሥነ-ሥርዓት ረቂቅ ደንብ ላይ ከፌዴሬሽን ምክር ቤት ጋር በመተባበር የግብዓት ማሰባሰቢያ የምክክር መድረክ በቢሾፍቱ አካሂዷል። የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አቶ አገኘሁ ተሻገር በዚሁ ጊዜ፤ ተቋሙ ሕገ-መንግሥታዊ ጉዳዮችን በሚመለከት የውሳኔ ሀሳቦችን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት አደራጅቶ በማቅረብ ውጤታማ ሥራ እየሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል። ዜጎች በፍትሕ የመዳኘትና የሚያቀርቡት የሕገ-መንግሥት ትርጉም ጥያቄም በቁጥርም ሆነ በፍላጎት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ገልጸው አሁን ላይም ከ100 በላይ የትርጉም ጉዳዮች መቅረባቸውን ጠቁመዋል። የዜጎች የሕገ-መንግሥት ትርጉም ጥያቄ እያደገ በመምጣቱ ለሚቀርቡ ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ ለመስጠት በትኩረት እየተሰራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። የፌዴሬሽን ምክር ቤትም የሚቀርቡ የሕገ-መንግሥት ትርጉም ጥያቄዎችን በሥርዓት ምላሽ ለመስጠት የአቤቱታና ቅሬታ አቀራረብ የሚመራበት መመሪያ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። የሕገ-መንግሥት አጣሪ ጉባኤ የአሰራር ሥነ-ሥርዓት ረቂቅ ደንብ ጸድቆ ወደ ሥራ ሲገባም ዜጎች ለሚያነሷቸው የሕገ-መንግሥት ትርጉም ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ መስጠት ያስችላል ብለዋል። የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንትና የሕገ-መንግሥት አጣሪ ጉባዔ ሠብሳቢ አቶ ቴዎድሮስ ምህረት፤ በሕገ-መንግሥቱ አንቀጽ 84 ንዑስ አንቀጽ ቁጥር 04 መነሻነት የሕገ-መንግሥት አጣሪ ጉባኤ የሚመራበት የአሰራር ሥነ-ሥርዓት ደንብ እንደሚዘጋጅ መመላከቱን ገልጸዋል። በፍርድ ቤቶች የፍትሐብሔርና የወንጀል ሥነ-ሥርዓት ደንብ እንዳለው ሁሉ የሕገ-መንግሥት አጣሪ ጉባኤም በሕገ-መንግሥቱ መነሻነት የአሰራር ደንብ እንዲኖረው ያዛል ብለዋል። በዚህ መነሻነት በረቂቅ ደረጃ የተዘጋጀው የአሰራር ሥነ-ሥርዓት ወደ ሥራ ሲገባ የሚቀርቡ የሕገ-መንግሥት ትርጉም አቤቱታዎችን በተሻለ ፍጥነት ውሳኔ ለመስጠት ዕድል እንደሚፈጥርም አንስተዋል። በዚህ ዓመትም 4 ሺህ የሚጠጉ ጉዳዮች ለሕገ-መንግሥት አጣሪ ጉባኤ ቀርበው እስከ ታኅሳስ መጨረሻ ድረስ በ1 ሺህ 19 ጉዳዮች ላይ ውሳኔ መሰጠቱን ገልጸዋል። በአጣሪ ጉባኤው ውስን የሕገ-መንግሥት ጥያቄዎችን እንደሚመለከት ጠቁመው፤ የፍርድ ቤት ውሳኔ ያገኙ ጉዳዮች ወደ አጣሪ ጉባኤው እንዳይመጡ ለማድረግ ኅብረተሰቡን የማስገንዘብ ሥራ ይሰራልም ብለዋል። በረቂቅ ደንቡ አስመልክቶ በቀረበው የመነሻ ጽሁፍ ላይ ከተሳታፊ አካላት ለተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል።
የኢትዮጵያ ሴቶች ፌዴሬሽን በአገሪቱ ሰላምን ለማፅናት ሴቶች የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲወጡ እየደገፈ ነው
Mar 15, 2024 214
አዳማ፤ መጋቢት 6/2016(ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ሴቶች ፌዴሬሽን በአገሪቱ ሰላምን ለማፅናት ሴቶች የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲወጡ እየደገፈ መሆኑን የኢትዮጵያ ሴቶች ፌዴሬሽን ገለጸ። ፌዴሬሽኑ ከሁሉም ክልሎችና ሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች ለተውጣጡ የፌዴሬሽኑ አመራር አባላት የአመራር ሰጪነት ሚና ላይ ያተኮረ የአቅም ማጎልበቻ ስልጠናና የስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በአዳማ ከተማ እያካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ሴቶች ፌዴሬሽን ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ወይዘሮ አስካለ ለማ እንደገለጹት፤ ፌዴሬሽኑ በአገሪቱ የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለመፍታት በሚደረገው እንቅስቃሴዎች ውስጥ ሴቶች የድርሻቸውን እንዲወጡ ይደግፋል። መድረኩ የተዘጋጀውም በተለይ ሴቶች በሰላም ግንባታ ወሳኝ ሚና እንዲጫወቱ የየክልሎቹ የፌዴሬሽን አመራር አባላት የማስፈጸም አቅማቸውን ለማጎልበት እንደሆነ ተናግረዋል። በዚህም በቂ የማስፈፀም ክህሎትና አቅም እንዲገነቡ ያለመ ግምገማ እንደሚካሄድ ያመለከቱት ወይዘሮ አስካለ ፤ በቀጣይ በአገር ሰላምና ፀጥታ ጉዳይ ላይ በየደረጃው የሚገኙ የሴቶች አደረጃጀቶች ከመንግሥት ጋር ተቀናጅተው በትብብር እንዲሰሩ ለማስቻልም ነው ብለዋል። እንዲሁም ሴቶች መልካም አስተደደር እንዲረጋገጥና የሴቶች የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት እንዲጠናከር በአቅም ማብቃት ላይም እየደገፉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በተለይ በየደረጃው ባለው መንግስታዊ መዋቅር ላይ ያሉ ሴቶች ፈጠራና ፍጥነት የታከለበት ሳይንሳዊ የአመራር ሰጪነት ሚና እንዲወጡም እንዲሁ። የኦሮሚያ ክልል ሴቶች ፌዴሬሽን ምክትል ፕሬዚዳንት ወይዘሮ ፀገነት ሃይሌ በበኩላቸው ፤መድረኩ የሴቶች የማስፈፀም አቅም የሚያጎለብት በተለይ በስራ ሂደት ውስጥ እያጋጠሙን ያለው የአመራር ሰጪነት ክፍተት የምንቀርፍበት ነው ብለዋል። በተጨማሪም የሴቶች አደረጃጀቶች በአገር ሰላምና ፀጥታ ማስፈን ረገድ የጎላ ሚና እንዲጫወቱ የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። የሃዳ ሲንቄ የሰላም ማህበር በማደራጀት በክልሉ የሚስተዋሉ የሰላምና ፀጥታ ችግሮችን ለመፍታት ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰው ፤ በተለይ የሴቶች አደረጃጀቶች ለሰላም ዘብ እንዲቆሙ እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ሴቶች ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ወይዘሮ ኢፍቱ አባስ ፤ በአስተዳደሩ ሰላምና ፀጥታን ለማስፈን በሚደረገው ጥረት ውስጥ ሴቶች ግንባር ቀደም ሚና እየተጫወቱ መሆኑን ተናግረዋል። በአለመግባባት በሚፈጠር ችግር የመጀመሪያው ተጎጂዎች ሴቶችና ህፃናት መሆናቸውን አውስተው፤ "ቡና ለሰላም " በሚል ሀሳብ ሰላም የዕለት አጀንዳቸው እንዲያደርጉ ማመቻቸታቸውን ገልጸዋል። ሰላም ልጆች ትምህርት ቤት መላክና ሰርቶ ለመለውጥ ብቻ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ መሆኑን አጀንዳ አድርገው በጎረቤት፣ በአካባቢና በቀበሌ ሰላም እንዲጠበቅ በትኩረት እየሰሩ እንደሚገኙ አብራርተዋል። የአቅም ማጎልበቻ ስልጠናውና የግምገማው መድረኩ ለአራት ቀናት እንደሚቆይ ተገልጿል።
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ስኬት ተመዝግቧል---አቶ ፀጋዬ ማሞ
Mar 15, 2024 211
ቦንጋ፤ መጋቢት 6/2016(ኢዜአ) ፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ባለፉት ሁለት ዓመታት በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች በተከናወኑ ሥራዎች ስኬት መመዝገቡን በብልጽግና ፓርቲ የክልሉ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ፀጋዬ ማሞ ገለጹ። "ቃልን በተግባር ለኢትዮጵያ ብልጽግና" በሚል መሪ ሀሳብ የክልሉ የብልጽግና ፓርቲ አባላት ኮንፈረንስ ለማካሄድ ቅድመ ዝግጅቱ መጠናቀቁም ተገልጿል። በብልጽግና ፓርቲ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ፀጋዬ ማሞ ዛሬ በሰጡት መግለጫ፣ ባለፉት ሁለት ዓመታት በክልሉ በተከናወኑ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ስኬት ተመዝግቧል። በተለይ ልማቶቹ የህዝብን ጥያቄ መመለስን ትኩረት ማድረጋቸውን ጠቅሰው፣ በቀጣይም ህዝብን በማሳተፍ የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል። በየደረጃው ከ535 ሺህ በላይ የፓርቲው አባላት የሚሳተፉበት ኮንፈረንስ ከመጋቢት 8 ቀን 2016 ጀምሮ ለሰባት ቀናት እንደሚካሄድም ተናግረዋል። መድረኩ በክልሉ በማህበራዊ እና በኢኮኖሚያዊ ዘርፎች የተከናወኑ ስራዎችና የተገኙ ስኬቶች በጋራ ከመገምገም ባለፈ ጉድለቶች የሚታረሙበት መሆኑንም ገልጸዋል። በኮንፈረንሱ በተለያዩ ዘርፎች ባለፉት ሁለት ዓመት ተኩል የተከናወኑ ተግባራትንና የተገኙ ውጤቶችን የሚያሳይ ሰነድ ቀርቦ ውይይት እንደሚደረግበት አመልክተዋል። አቶ ፀጋዬ እንዳሉት እንደ ክልል በርካታ የህዝብ ጥያቄ የሆኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጉዳዮችን ለመመለስ የሚያስችሉ ሥራዎች ቢከናወኑም ከችግሩ ስፋት አንፃር ቀሪ ተግባራት አሉ። በተለይ የክልሉን ሰላም አስተማማኝ ከማድረግ አንፃር በተሰሩ ሥራዎች የመጣውን ውጤት በማጠናከር ክልሉን የዕድገት ማሳያ ለማድረግ ይሰራል ብለዋል። የህዝብን ተጠቃሚነት ለማከናወን የሚሰሩ ሥራዎችን በዘላቂነት ለማስቀጠል የአመራሩን አቅም መገንባት ወሳኝ ነው ያሉት አቶ ፀጋዬ፣ "ከዕዳ ወደ ምንዳ" በሚል ርዕስ ለፓርቲ አባላትና አመራሮች ስልጠና መሰጠቱን ገልጸዋል። ከዚህ ባለፈ በህዝባዊ ውይይት የተነሱ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን በቅደም ተከተል ለመፍታት የሚያስችል እንቅስቃሴ ተጀምሯል ብለዋል። በተግባር የመፈጸምና የማስፈጸም አቅም ያለውን ጠንካራ አመራር ማፍራትና ድክመት በታየባቸው ላይ የእርምት እርምጃዎች የመውሰድ ሥራም እየተሰራ ነው ሲሉ ገልጸዋል። ኮንፍረንሱ ህብረ ብሔራዊ አንድነትን ለማጠናከር ጠቀሜታ እንዳለው ገልጸው፣ ለኮንፈረንሱ ውጤታማነትም አመራሩና አባላት የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርጉ አስገንዝበዋል።
ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ የ6 አገራት አምባሳደሮች የሹመት ደብዳቤ ተቀበሉ
Mar 15, 2024 210
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 6/2016(ኢዜአ)፦ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ በኢትዮጵያ የተሾሙ የ6 አገራትን አምባሳደሮች የሹመት ደብዳቤ ዛሬ ተቀብለዋል። ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ የሹመት ደብዳቤያቸውን የተቀበሏቸው አምባሳደሮች የማሊ፣ የሕንድ፣ የደቡብ ሱዳን፣ የቦትስዋና፣ የኬፕ ቬርዴና የጃማይካ አገራት ናቸው። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ ትናንትና ዛሬ የ17 አገራት አምባሳደሮች የሹመት ደብዳቤዎች ማቅረባቸውን ተናግረዋል። ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ ከሁሉም አምባሳደሮች ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ኢትዮጵያ ከአገራቱ ጋር ያላትን የሁለትዮሸ ግንኙት ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ውይይት መደረጉን ገልፀዋል። በውይይታቸው አምባሳደሮቹ በአገራቱ መካከል የተደረሱ ሥምምነቶች ተግባራዊ እንዲሆኑና በተለይም በአዳዲስ የንግድና ኢንቨስትመንት አጋርነቱን ለማጠናከር በትኩረት እንዲሰሩ ጠይቀዋል። በጋራ መሥራት በሚያስፈልጉ በባለብዙ መድረኮችም ግንኙነቱን ለማጠናከር ትኩረት አድርገው እንዲሰሩም ፕሬዚዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ ጥሪ ማቅረባቸው አምባሳደር ብርቱካን ተናግረዋል።