ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
የዓድዋ ድል የአፍሪካውያን የጋራ የነፃነት ቀንዲል ነው
Mar 1, 2026 111
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፡- የዓድዋ ድል የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የመላው ጥቁር ሕዝቦችና የአፍሪካውያን የጋራ ድል መሆኑን የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ሚኒስትሮችና ከፍተኛ የመከላከያ አመራሮች ገለጹ። የዓድዋ ድል ለአፍሪካዊያን የጋራ ደኅንነትና ወታደራዊ ትብብር ትልቅ መሠረት ነው ሁለተኛው የአፍሪካ መከላከያ ሚኒስትሮች ኮንፈረንስ “ከአኩሪ ታሪክ፣ ወደ ብሩህ አድማስ” በሚል መሪ ሀሳብ ተካሂዷል፡፡ በጉባኤው ላይ የተገኙት ሚኒስትሮችና ወታደራዊ መሪዎች እንዳሉት፤ የዓድዋ ድል ለአህጉራዊ አንድነትና ልማት ትልቅ ትምህርት የሚቀሰምበት መሆኑን አረጋግጠዋል። የአህጉሪቷን ውስብስብ ስትራቴጂካዊ ሁኔታ ለመቋቋም ወታደራዊ ትብብርን ማጠናከር፣ መረጃ መለዋወጥና ጥረቶችን ማቀናጀት ወሳኝ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ የኬንያ መከላከያ ሚኒስትር ሶልፐን ቱያ እንዳሉት፤ የዓድዋ ድል የኢትዮጵያ ታሪክ ብቻ ሳይሆን የመላው ጥቁር ሕዝብ የማንነትና የነፃነት አርማ ነው፡፡ ድሉ በአውሮፓውያን የቅኝ አገዛዝ ቀንበር ስር ለነበሩ አፍሪካውያን የይቻላል የተስፋ ብርሃን የፈነጠቀና ለፓን-አፍሪካዊነት እንቅስቃሴ መሠረት የጣለ ታላቅ ክስተት መሆኑን ተናግረዋል። ዓድዋን ወደ ኋላ የምናይበት ታሪክ ብቻ ሳይሆን ወደ ፊት የምንመለከትበት መነጽር ሊሆን ይገባል ያሉት ሚኒስትሯ ፤ የዓድዋ ድል መሠረት ጽኑ አንድነትና የማይበገር የሀገር ፍቅር መሆኑን አስገንዝበዋል። የደቡብ ሱዳን የመከላከያ እና የቀድሞ የጦር አርበኞች ጉዳይ ሚኒስትር ሌተናል ጄነራል ቾል ቶን ባሎክ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ ከ130 ዓመታት በፊት በዓድዋ የሰው ልጅ እኩልነትን በተግባር ያሳየችበት ነው ብለዋል፡፡ ይህም ለአፍሪካ የነፃነት ንቅናቄ መሠረት መሆኑን ጠቅሰው፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካውያንን መንፈስና ጥንካሬ ዳግም የቀሰቀሰች ታሪካዊ ሀገር መሆኗንም አክለዋል። የዚምባብዌ የመከላከያ ምክትል ሚኒስትር ብሪጋዴር ጄኔራል ሌቪ ማዪህሎሜ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ድሉን የተቀዳጀችው በማንም ድጋፍ ሳይሆን በአገራዊ አንድነቷ መሆኑ ለሌሎች አገራት ትልቅ ኩራት ነው። ይህ ነፃነትን በራስ ጥረት ማስጠበቅ ዛሬም ቢሆን ታላላቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶችን በራስ አቅም ለመገንባትና በኢኮኖሚ ራስን ለመቻል ለሚደረገው ጥረት እንደ ትልቅ መነሳሳት እንደሚቆጠር ገልጸዋል። የዛምቢያ መከላከያ ኃይል አዛዥ ጄኔራል ጆፍሪ ሲቶንጎ ዚዬሌ፤ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ድሉን ከዘመናዊው የልማት ጉዞ ጋር በማያያዝ እያሳየች ያለችው ስኬት የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም፣ በመሠረተ ልማት ግንባታ፣ በኢነርጂ ዘርፍ መስፋፋት እና በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) ቴክኖሎጂ አጠቃቀም ረገድ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ አርአያ መሆኗን ገልጸዋል። የዓድዋ ድል ትናንት ነፃነትን እንዳመጣ ሁሉ ዛሬ ደግሞ ለአፍሪካ ብልጽግና እና ሰላም መከበር እንደ ዋነኛ መነሳሻ ሊያገለግል እንደሚገባ በኮንፈረንሱ ላይ ተመልክቷል።
የዓድዋ ድል ሲከበር ለዘላቂ ሰላምና ልማት በበለጠ በመትጋት ሊሆን ይገባል
Mar 1, 2026 74
ደብረ ማርቆስ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የዓድዋ ድል ሲከበር ዘላቂ ሰላምና ልማት ለማስመዝገብ የበለጠ በመትጋት ሊሆን እንደሚገባ ተመለከተ ። በደብረ ማርቆስ ከተማ 130ኛው የዓድዋ ድል መታሰቢያ በአል ተከብሯል። የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ተሾመ ዋለ ፤ የዓድዋን ድል ስናከብር የራሳችንን ታሪክ በመስራት መሆን አለበት ብለዋል። በተለይም ሰላምን ዘላቂ ለማድረግና ልማትን ለማስቀጠል የበለጠ መትጋት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። አባቶች በዓድዋ ድል ያሳዩትን የሀገር ፍቅርና አንድነት በማስቀጠል ለዘላቂ ሰላምና ልማት መትጋት ይገባል የዓድዋ ድል የተገኘው በሁሉም ኢትዮጵያዊያን ትብብርና አንድነት መሆኑን ጠቁመው በተለይም የቀድሞ አባቶችን ጥበብና ስልት በመላበስ ለልማትና ሰላም መትጋት ይገባል ብለዋል። የከተማ አስተዳደሩ ሴቶችና ወጣቶች መምሪያ ሃላፊ ወይዘሮ ፈንታነሽ አፈወርቅ በበኩላቸው፤ ቀደምት አባቶች በደምና በአጥንታቸው አስከብረዋት ያኖሯትን ሀገር የአሁኑ ትውልድ ከነሙሉ ክብሯ ማስቀጠል አለበት ብለዋል። ለዚህም ሴቶችና ወጣቶች የልማትና የሰላም ተምሳሌት በመሆን ድህነትን ታሪክ ለማድረግ በሚሰራው ስራ ግንባር ቀደም ተዋናይ መሆን እንዳለባቸው አስገንዝበዋል ። ከተሳታፊዎች መካከል ወጣት ህይወት ግዛቸው፤ አባቶቻችን ያስረከቡንን ሀገር ካደጉ ሀገራት ተርታ ለማሰለፍ የበኩላችንን እንወጣለን ብላለች። ዓድዋን ስንዘክር በሰላምና ልማት ስራዎች በበለጠ በመሳተፍ ስኬት ለማስመዝገብ ቃል በመግባት ነው ያለው ደግሞ ወጣት የሽዋስ ይበልጣል ነው። በበአሉ ላይ የከተማ አስተዳደሩ አመራር አካላት፣ ወጣቶች ሴቶችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
ዓድዋ በመልካምነት የተባበሩ ልቦች፣ በኅብረት የተሰለፉ ጀግኖች ድል ያስመዘገቡበት የጽኑ መንፈስና የከፍታችን ተምሳሌት ነው
Mar 1, 2026 90
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ ዓድዋ በመልካምነት የተባበሩ ልቦች፣ በፍቅር ጉልበት የበረቱ ክንዶች፣ በኅብረት የተሰለፉ ጀግኖች ድል ያስመዘገቡበት የጽኑ መንፈስና የከፍታችን ተምሳሌት ነው ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለ130ኛው የዓድዋ ድል በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ የእንኳን አደረሳችሁ ሙሉ መልዕክቱ እንደሚከተለው ቀርቧል፡- ዓድዋ የጥቁር ሕዝቦች የድል አክሊል! የዓድዋ ጦርነት ሁሉም ኢትዮጵያውያን ልዩነቶቻቸውን ወደ ጎን ትተው፣ በአንድነት የተሰለፉበትና ድል ያደረጉበት የወል እውነት፣ የወል ክብር፣ የወል ታሪካችን ነው። ዓድዋ በመልካምነት የተባበሩ ልቦች፣ በፍቅር ጉልበት የበረቱ ክንዶች፣ በኅብረት የተሰለፉ ጀግኖች ድል ያስመዘገቡበት የጽኑ መንፈስና የከፍታችን ተምሳሌት ነው። ከዓድዋ የምንማረው ታላቅ እውነትና የወል ውርስ አንድ ስንሆን ማሸነፍ እንደምንችል ነው። በዚህ በማይደበዝዝ ዘለዓለማዊ የድል ማኅተም፣ ጀግኖች አባቶቻችንና እናቶቻችን ሀገርን ከነሙሉ ክብሯ ለኛ ዘመን አሸጋግረዋል። በደም በጻፉት ደማቅ የታሪክ ድርሳን ለሀገር ፍቅርና ክብር መሥዋዕት መሆን ምን ማለት እንደሆነም በተግባር አስተምረውናል። ሀገራችን በልጆቿ ጠንካራ አንድነት አያሌ ፈተናዎችን ተሻግራለች፤ በኅብረ ብሔራዊ አንድነታችን ስንቆም ዓለምን ያስደመሙ ድሎችን መፈጸም እንደምንችልም በተደጋጋሚ አሳይተናል። ዛሬም ጠንካራና የታፈረች ኢትዮጵያን ለመገንባት በጋራ ጉዳዮች ላይ መግባባትና ከአጽናፍ እስከ አጽናፍ ገንቢ ሚናችንን መወጣት ይገባናል። በሁሉም ብሔር ብሔረሰቦች ውስጥ ያሉ እምቅ ጥበቦች፣ ዕውቀቶችና እሴቶችን በመቀመር ለሀገር የከፍታ ጉዞ ልንጠቀምባቸው ያስፈልጋል። በወል ጉዳዮች መግባባት ስንፈጥር የሚኖረን የተደመረ ዐቅም፣ ከልዩነት ፖለቲካ ወደ አንድነት፣ ከድህነት ወደ ብልጽግና የምናደርገውን ጉዞ ያፋጥነዋል። ዓድዋ የድል አክሊላችን ነው ስንል፣ ያለፈውን ውድ ታሪካችንን ከዛሬና ከነገ የምንገምድበት ክር፣ በሁሉም መስክ የታፈረችና የኮራች ሀገርን የምንገነባበት ጽኑ መሠረት ስለሆነም ጭምር ነው።
ዓድዋን ከትናንት አሸናፊነት ባሻገር ለዛሬ ሀገራዊ ግንባታና ለነገ ብሔራዊ ኩራት ልንጠቀመው ይገባል
Mar 1, 2026 134
ወላይታ ሶዶ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ ዓድዋን ከትናንት አሸናፊነት ባሻገር ለዛሬ ሀገራዊ ግንባታና ለነገ ብሔራዊ ኩራት ልንጠቀመው እንደሚገባ ተመላከተ። ኢትዮጵያን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘው ግብ እውን እንዲሆን ወጣቱ በአርበኝነት ስሜት ሊተጋ ይገባል የወላይታ ዞን እና የወላይታ ሶዶ ከተማ አስተዳደር በጋራ የ130 ኛውን የዓድዋ ድል መታሰቢያ በዓል በወላይታ ሶዶ ከተማ በተለያዩ ዝግጅቶች አክብረዋል። በመድረኩም በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ አቶ ተፈሪ አባተ፤ የዓድዋ ድል መታሰቢያ በየዘርፉ ለምናስመዘግበው ሁለንተናዊ ልማት የሥነ-ልቦና ስንቅ ይሆናል ብለዋል። አቶ ተፈሪ አክለውም ዓድዋን ከትናንት አሸናፊነት ባሻገር ለዛሬ ሀገራዊ ግንባታና ለነገ ብሔራዊ ኩራት ልንጠቀመው እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ወጣቱ ትውልድ ጀግኖች አባቶች በዓድዋ ያሳዩትን ገድል የሀገራችንን ሁለንተናዊ ሰላምና ልማት በማጽናት ሊደግመው ይገባል ብለዋል። የወላይታ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ሳሙኤል ተሰማ (ረ/ፕሮፌሰር) በበኩላቸው፤ የዓድዋ ድል የብዝሃነትና የመቻቻል፣ የፅናትና የቆራጥነት ተምሳሌትና የአንፀባራቂ ጀግንነት ውጤት ነው ብለዋል። የዓድዋ ድል መላው ኢትዮጵያውያን ወራሪውንና ተስፋፊውን ኃይል ተከላክለው አኩሪ ተጋድሎ ያደረጉበት መሆኑ አውዱን ልዩ ያደርገዋል ብለዋል። የአሁኑ ትውልድ ደግሞ ጀግኖች አባቶቻችን በዓድዋ ተራሮች ባደረጉት ተጋድሎ ሀገራችን በዓለም አቀፍ ደረጃ የተጎናጸፈችውን ክብርና ዝና እንደ ወኔ በመታጠቅ ብሔራዊ ጥቅሟን የማስከበር ኃላፊነቱን መወጣት እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡ የዓድዋ ድል ታሪካዊ ድላችን ብቻ ሳይሆን የአንድነት፣ የአብሮነትና የመተባበር ኃይል ምን ያህል ለስኬት እንደሚያበቃ ትምህርት የወሰድንበት ነው ያሉት ደግሞ የወላይታ ሶዶ ከተማ ከንቲባ ወይዘሮ እታገኝ ኃይለማርያም ናቸው። የዓድዋ ድል አልሸነፍ ባይነት ስነ-ልቦናን የተላበስንበት ድል ነው ያሉት ወይዘሮ እታገኝ የከተማዋ ነዋሪዎችም የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ከግብ በማድረስና ለመጪው ትውልድ ውብና ምቹ ከተማን በማውረስ ሊደግሙት እንደሚገባም ገልጸዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር የስራ ኃላፊዎች፣ የሰራዊት አባላት እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘው ግብ እውን እንዲሆን ወጣቱ በአርበኝነት ስሜት ሊተጋ ይገባል
Mar 1, 2026 79
ሆሳዕና ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘው ግብ እውን እንዲሆን ወጣቱ በአርበኝነት ስሜት ሊተጋ እንደሚገባ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ገለፁ፡፡ ብልፅግና ፓርቲ ዋና መገለጫው ለሕዝብ የገባውን ቃል በተግባር በመፈጸም ውጤት ማስመዝገብ ነው 130ኛውን የዓድዋ ድል መታሰቢያ በዓል ምክንያት በማድረግ" የዓድዋ አደራ አንድነት፣ ሉዓላዊነትና ማንሰራራት" በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ ክልል አቀፍ የወጣቶች መድረክ በሆሳዕና ከተማ ተካሄዷል፡፡ ርዕሰ መስተዳድሩ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት፣ የዓድዋ ድል የመላው ጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ምልክትና ዓለም አቀፋዊ እውቅና ያለው የታሪክ አሻራ መሆኑን ገልጸዋል። የአሁኑ ዘመን የአርበኝነት ትግል ከድህነት ጋር መሆኑን ጠቅሰው፣ ወጣቱ ይህንን ለማሸነፍ በቁርጠኝነት ሊነሳ ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያን የብልጽግና ተምሳሌት ለማድረግ የተያዘው ግብ እውን ሊሆን የሚችለው ወጣቱ በታታሪነትና በአርበኝነት ስሜት ሲሰራ መሆኑንም አመልክተዋል። የክልሉ የወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ ጌታቸው ሌሊሾ በበኩላቸው፣ የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያንን በአንድነት ጥላ ስር በማሰባሰብ የተገኘ አኩሪ ገድል ነው ብለዋል። የምክክር መድረኩ ዋና ዓላማ የዓድዋን ስኬት በወጣቱ ውስጥ ማስረጽና ወጣቱን የታሪክ ባለቤትና የልማት ኃይል ማድረግ ነው ብለዋል። ወጣቶች ቀደምት አባቶች በዓድዋ የከፈሉትን መስዋዕትነትንና የተገኘውን ድል በክልሉ ፈጣንና ሁለንተናዊ ዕድገት ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የራሳቸውን አሻራ በማኖር ሊደግሙ ይገባል ብለዋል።፡ በመድረኩ የተሳተፉ ወጣቶች የቀደምት አባቶችን የዓድዋ ድል መስዋዕትነት በልማት ለመድገም ያላቸውን ዝግጁነት ገልጸዋል። ወጣት አብዱወሀብ ኑረዲን፤ ከጀግኖች አባቶች የተረከብናትን ሀገር ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ ገዢ ትርክትን መገንባትና ህብረ ብሔራዊ አንድነትን ማጠናከር የወቅቱ አርበኝነት ነው ሲል ተናግሯል።
የዐድዋ ድል የኢትዮጵያውያንን የማይቀየር ዐቋምና ዐቅም ያሳየ ድል ነው
Mar 1, 2026 120
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የዐድዋ ድል የኢትዮጵያውያንን የማይቀየር ዐቋምና ዐቅም ያሳየ ድል ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለ130ኛው የዐድዋ ድል በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ሙሉ መልዕክት እንደሚከተለው ቀርቧል፡- እንኳን ለ130ኛው የዐድዋ ድል በዓል አደረሳችሁ። የዐድዋ ድል የኢትዮጵያውያንን የማይቀየር ዐቋምና ዐቅም ያሳየ ድል ነው። ኢትዮጵያውያን በሀገራቸው ብሔራዊ ጥቅም፣ ነጻነትና ሉዓላዊነት ላይ የማይቀየር ዐቋም አላቸው። ይሄንን ዐቋማቸውን በጽኑ መሠረት ላይ ለመትከል ደግሞ ሁሉንም አቅማቸውን ይጠቀማሉ። ሥርዓታትና መሪዎች ሊቀየሩ ይችላሉ፤ በአንዳንድ ጉዳዮች ልዩነቶች ይኖሯቸው ይሆናል፤ ስለ ሀገራቸው ያላቸው ዐቋምና ለሀገራቸው የሚያወጡት አቅም ግን አይቀየርም። ወደ ዐድዋ የዘመቱ ጀግኖቻችን ሁሉ በሁሉም ነገር የተስማሙ አይደሉም። አንድ ዓላማ ነበራቸው እንጂ አንድ ዓይነት አልነበሩም። አንድ ሀገር ነበራቸው እንጂ አንድ ባህልና እምነት አልነበራቸውም። በዚያ ጊዜ ሀገራቸውን ከድተው ከጠላት ጋር ያበሩ ባንዳዎች ነበሩ። ለጊዜያዊ ጥቅም ሲሉ ዘላቂ የሀገራቸውን ጥቅም የሸጡ ምንደኞችም ነበሩ። ከባዳ ጋር ወግነው ወገናቸውን ያስማሙ ደላሎችም ነበሩ። ጀግኖች እናቶቻችን እና አባቶቻችን የተዋጉት ከወራሪው የጣሊያን ጦር ጋር ብቻ አልነበረም። ከምንደኞች፣ ከባንዳዎች እና ከሀገር ደላሎች ጭምር እንጂ። ዐርበኝነት ማለት ባዳና ባንዳን ማሸነፍ ማለት ነው። ዐርበኝነት ማለት ለሀገር ጥቅም ሲባል የግል ጥቅምን ማሸነፍ ማለት ነው። ዐርበኝነት ማለት ለሀገር ክብር ሲባል የራስን ክብር መሠዋት ነው። የዐድዋ ድል በዓል እነዚህን ሁሉ የምናስታውስበት ነው። የዐድዋ ድል በዓል የኢትዮጵያውያንን ዐቅምና አቋም እንደገለጠው ሁሉ ዛሬም በጸና አቋም፣ የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ዐቅም የምንገልጥበት ጊዜ ነው። በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በቱሪዝም፣ በማዕድን እና በዲጂታል ሀገራችን ያላትን ዐቅም መግለጥ አለብን። የዐድዋን ድል በሁሉም ዘርፍ ለመድገም፣ የኢትዮጵያ ዐቅም ጽኑ መሠረት ሊኖረው ይገባል። ሀገርን ዐቅም ያሳድጋታል፤ ዐቅም ይገነባታል። ሀገርን ዐቅም ይሠራታል። ዐቋም ያጸናታል። ሀገርን ዐቅም ያራምዳታል፤ ዐቋም ያሻግራታል። የዐድዋ ድል በዓላችን የኢትዮጵያን ዐቅም ይበልጥ የምንገነባበትና የኢትዮጵያውያንን ዐቋም ይበልጥ የምናጸናበት እንደሚሆን ተስፋ አደርጋለሁ። ኢትዮጵያ በልጆቿ ጥረት ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር!! ፈጣሪ ኢትዮጵያና ሕዝቦቿን ይባርክ! የካቲት 22 ቀን 2018 ዓ.ም
ኮሚሽኑ እስካሁን ያከናወናቸው ተግባራት ለምክክሩ ውጤታማነት መሠረት የሚጥሉ ናቸው - የፖለቲካ ፓርቲዎች
Mar 1, 2026 105
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን እስካሁን ያከናወናቸው ተግባራት ለምክክሩ ውጤታማነት መሠረት የሚጥሉ መሆናቸውን የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ገለጹ። ሀገራዊ ምክክሩ የሰለጠነ የፖለቲካ ባህል ለማዳበር ቁልፍ ሚና ይጫወታል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5ኛው የሥራ ዘመን 1ኛ አስቸኳይ ስብሰባው የኮሚሽኑን የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት መገምገሙና ቀሪ ሥራዎችን ለማከናወን የቀረበለትን የጊዜ ማራዘሚያ የውሳኔ ሐሳብ በሙሉ ድምፅ ማጽደቁ ይታወቃል። በዚህም ለተጨማሪ ስምንት ወራት መራዘሙ የሚታወቅ ሲሆን የተጀመሩ ሥራዎችን ለማጠናቀቅ ፋይዳው የጎላ መሆኑ ተመላክቷል፡፡ ይህንኑ ውሳኔ አስመልክቶ ኢዜአ ያነጋገራቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች ኮሚሽኑ የጀመራቸውን ስራዎች በአግባቡ እንዲያጠናቅቅና አካታችነትን ይበልጥ እንዲያረጋግጥ የስራ ጊዜው መራዘሙ ተገቢ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልና የምርጫ ኃላፊ አቶ እዮብ መሳፍንት፤ አገራዊ ምክክሩ ለኢትዮጵያ መጻኢ እድል ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ውጤታማና ትክክለኛ ምክክር እንዲካሄድ ከማድረግ አንጻር የተጨመረው ጊዜ ለምክክሩ ስኬት ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል። ኮሚሽኑ እስካሁን ያከናወናቸው ተግባራት የሚታዩና ለምክክሩ ውጤታማነት መሠረት የሚጥሉ መሆናቸውን ፓርቲያቸው እንደሚያምን ገልጸዋል። ኢዜማ እስካሁን ሲያደርግ የነበረውን ድጋፍ አጠናክሮ በመቀጠል በቀጣይ የኮሚሽኑ ሥራዎች ላይ የድርሻውን ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል። የአዲስ ትውልድ ፓርቲ ፕሬዝዳንት አቶ ሰለሞን ታፈሰ፤ አገራዊ ምክክሩ በዜጎች መካከል ለዘመናት የቆዩ ስብራቶችን ለመጠገን ትልቅ ዕድል መሆኑን ጠቁመዋል። ኮሚሽኑ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ ተስፋ ሰጪ ሥራዎችን ሲያከናውን የቆየ መሆኑን ጠቅሰው የምክር ቤቱ የጊዜ ማራዘሚያ ውሳኔ ቀሪ ሥራዎች በጥራትና በውጤታማነት እንዲከናወኑ ታሳቢ ያደረገ ነው ብለዋል። ፕሬዚዳንቱ አክለውም የሁሉንም ዜጎች ድምፅና ተሳትፎ ለማካተት ጊዜ ወስዶ መሥራት አማራጭ የሌለው ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል። ዜጎች በሂደቱ ላይ የጣሉት ተስፋ እውን እንዲሆን ሁሉም የማህበረሰብ ክፍሎችና የሚመለከታቸው አካላት በቅንጅት መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል።
ሀገራዊ ምክክሩ የሰለጠነ የፖለቲካ ባህል ለማዳበር ቁልፍ ሚና ይጫወታል
Mar 1, 2026 134
ሰመራ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ሀገራዊ ምክክሩ ችግሮችን በውይይት ለመፍታትና የሰለጠነ የፖለቲካ ባህል ለማዳበር ቁልፍ ሚና እንዳለው የኢትዮጵያ ሴቶች ፌዴሬሽን አስታወቀ። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የካቲት 11 ቀን 2018 ዓ.ም ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽንን የሥራ ዘመን ለስምንት ወራት ማራዘሙ ይታወሳል። የሀገራዊ ምክክር ሂደቱን በስኬታማነት ለማስቀጠል የሁሉም አካላት ሚናና ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል ኮሚሽኑ በእነዚህ ጊዜያት ለማከናወን ከያዛቸው ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል በትግራይ ክልል የምክክር ሂደት ማከናወን፣ እስካሁን የተሰበሰቡ አጀንዳዎችን በየፈርጁ ለይቶ ማዘጋጀትና ለሕዝብ ይፋ ማድረግ ይገኙበታል። ለሀገራዊ ምክክር ጉባኤው የሚሆኑ አወያዮችና አመቻቾችን መለየትና አስፈላጊውን ስልጠና መስጠት፣እንዲሁም ሁሉንም ድምጾች የሚያስተናግድ፣ አሳታፊና አካታች ሀገራዊ የምክክር ጉባኤን ማካሄድ ተጠባቂ ሥራዎች ናቸው። ከምክክሩ የሚገኙ ውጤቶችን በማጠናቀር የመፍትሔ አቅጣጫዎችን ማዘጋጀትና አፈጻጸማቸውን መከታተል እንዲሁም ሀገር አቀፍ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን ማስፋትና የዶክመንቴሽን ሥራዎችን በዘመናዊ የዲጂታል ዘዴ ማደራጀትም ኮሚሽኑ በቀሪ የሥራ ዘመኑ የሚከውናቸው ተግባራት ናቸው። ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የሴት አደረጃጀት የሥራ ሃላፊዎች ሴቶች ለሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማነት በንቃት እየተሳተፉ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሴቶች ፌዴሬሽን ዳይሬክተር ገነት ስዩም እንዳሉት፣ሀገራዊ ምክክሩ የኢትዮጵያ የቆዩ ችግሮች በሰለጠነ መንገድ በውይይት እንዲፈቱና ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ ቁልፍ ሚና ይጫወታል። ሀገራዊ ምክክሩ የኢትዮጵያን ዘላቂ ሰላምና ልማት ለማረጋገጥ ያለውን ሚና በመገንዘብ በምክክር ሂደቱ ከከተማ እስከ ገጠር ያሉ ሴቶች በንቃት እንዲሳተፉና ፍላጎቶቻቸው በአጀንዳው እንዲካተት መደረጉንም ተናግረዋል። የአፋር ክልል ሴቶች ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ፋጡማ ሐንፈሬ በበኩላቸው፣ ፌዴሬሽኑ ከሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት የሴቶችን መሰረታዊ ችግሮች የመለየትና ዋና ዋና አጀንዳዎችን አደራጅቶ ለኮሚሽኑ የማቅረብ ስራ መሰራቱንም አስታውቀዋል። በሀገራዊ ምክክሩ ሴቶች ተሳታፊ ከመሆን ባለፈ በወሳኝ ጉዳዮች ላይ ያላቸው ሚና ጎልቶ እንዲወጣና በውሳኔ ሰጪነት እንዲሳተፉ እየተደረገ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የፌዴሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት ፎዚያ አብዱ ናቸው። ሀገራዊ ምክክሩ ችግሮች በውይይት እንዲፈቱና የሰለጠነ የፖለቲካ ባህል እንዲዳብር ቁልፍ ሚና ይጫወታል ብለዋል።
የዓድዋ ድል ለሀገራዊ ማንሰራራትና ለዘመናዊ አርበኝነት ስንቅ ነው-ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው
Mar 1, 2026 62
ባህርዳር፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦የዓድዋ ድል ለሀገራዊ ማንሰራራትና ለዘመናዊ አርበኝነት ስንቅ መሆኑን የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው ገለጹ። የዓድዋ ድል ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካውያን የተስፋ ብርሃን የፈነጠቀ ድል ነው የባህርዳር ከተማ አስተዳደር 130ኛ ዓመት የዓድዋ ድል በዓልን "የዓድዋ እሴት ለሁለንተናዊ ሀገራዊ ማንሰራራት" በሚል መሪ ሃሳብ በተለያዩ ዝግጅቶች አክብሯል። በበዓሉ የተገኙት የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ጎሹ እንዳላማው፣ የዓድዋ ድል የጀግንነት ታሪክ ብቻ ሳይሆን ለትውልዱ አንድነትን፣ ጽናትና ጥንካሬን ያስተማረ ነው ብለዋል። ድሉ ኢትዮጵያውያን ለሀገር ክብር ሲሉ ከሕይወት መስዋዕትነት እስከ አካል መጉደል ዋጋ በመክፈል ሉዓላዊነታቸውን ያጸኑበት የታሪክ አሻራ መሆኑን አንስተዋል። ልዩነቶችና የግል ፍላጎቶች ከሀገር ሉዓላዊነት በታች መሆናቸውን ያረጋገጠ፣ አርአያነት ያለው የተጋድሎ ስኬት መሆኑንም አመልክተዋል። የዓድዋ ድል ለሀገራዊ ማንሰራራትና ለዘመናዊ አርበኝነት ስንቅ መሆኑን ጠቅሰው፣ ወጣቱ ትውልድ የድሉን ምስጢር በመመርመር አሁን እያጋጠሙ ላሉ ችግሮች በሀገር ፍቅር ስሜት መፍትሄ ሊሰጥ ይገባል ብለዋል። ትውልዱ የአባቶቹን የዓድዋ አደራ በማንገብ ለሰላም፣ ለዕድገትና ለሀገራዊ ብልጽግና በአንድነት እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል። በበዓሉ ጥናታዊ ጽሁፍ ያቀረቡት የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ መምህር ገረመው እስከዚያው (ዶ/ር) የዓድዋ ድል በእብሪት የተሞላውን የነጮች የበላይነት የገታ ዓለም አቀፋዊ ክስተት መሆኑን አብራርተዋል። ትውልዱ ከበዓል አከባበር ባለፈ የቆራጥነትና የአልገዛም ባይነት ወኔን ተላብሶ በልማት ሥራዎች ላይ በንቃት ሊሳተፍ ይገባል ብለዋል።
የዓድዋ ድል ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለመላው አፍሪካውያን የተስፋ ብርሃን የፈነጠቀ ድል ነው
Mar 1, 2026 74
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የዓድዋ ድል ኢትዮጵያ ቅኝ ገዢን ድል በማድረግ ለአፍሪካውያን የነፃነት ተስፋን ያበሰረችበት ታሪካዊ ክስተት መሆኑን የዩኔስኮ የሰላም ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ጋይ ጆከን ገለጹ፡፡ ወጣቶች ከዓድዋ አባቶች የወረሱትን የአይበገሬነት እሴት በልማት መድገም ይጠበቅባቸዋል የዓድዋ ድል ኢትዮጵያውያን በአንድነት መንፈስ ቆመው የሀገራቸውን ሉዓላዊነት ያስከበሩበትና ለመላው ጥቁር ሕዝብ የነፃነት ፋና ወጊ የሆነ ታላቅ ድል ነው። የካቲት 23 ቀን 1888 ዓ.ም ኢትዮጵያውያን ለአንድ የጋራ ሀገራዊ ዓላማ በመሰለፍ ሀገሪቱን ለመውረር የመጣውን የጣሊያን ጦር ድል በማድረግ የማይረሳ አኩሪ ገድል የፈጸሙበት ዕለት ነው። ይህ ታሪካዊ ድል በየዓመቱ በደመቀ ሁኔታ የሚከበር ሲሆን ዘንድሮም 130ኛው የዓድዋ ድል በዓል "አኩሪ ታሪክ ወደ ብሩህ አድማስ" በሚል መሪ ቃል ይከበራል። የዩኔስኮ የሰላም ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ጋይ ጆከን ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በቅኝ ሊገዛት የመጣውን ኃይል ድል ያደረገች ብቸኛ ሀገር በመሆኗ መላው አፍሪካዊ ሊያውቀውና ሊኮራበት የሚገባ ታሪክ አስመዝግባለች። የአፍሪካ ሕብረት ምስረታ በአዲስ አበባ መደረጉ በአጋጣሚ የሆነ ሳይሆን ኢትዮጵያ በታሪክ ያላት ጉልህ አሻራ ውጤት መሆኑን ዳይሬክተሩ አስረድተዋል። ኢትዮጵያ ከዓድዋ ድል ባለፈ በአፍሪካ ሕብረት ምስረታ ውስጥ በነበራት ንቁ ተሳትፎ ለፓን አፍሪካኒዝም እሳቤ መጎልበት ትልቅ መሠረት የጣለች ሀገር መሆኗንም ጠቁመዋል፡፡ አፍሪካ የኃያላን አገራትን ትኩረት እየሳበች መምጣቷን አንስተው አህጉሪቱ ያላትን ሰፊ የተፈጥሮ ሀብትና የሰው ኃይል በአግባቡ በመጠቀም በዓለም አቀፍ መድረክ ተገቢውን ስፍራ የምትይዝበት ወቅት አሁን እንደሆነ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በልማት ዘርፍ ለአፍሪካ አርአያ በመሆን በኢኮኖሚው መስክ ዳግም ዓድዋን ለመድገም የምታደርገው ጥረት ለአህጉሪቱ ትልቅ ተስፋ መሆኑን ጠቁመዋል።
የዓድዋ ድል ለአፍሪካዊያን የጋራ ደኅንነትና ወታደራዊ ትብብር ትልቅ መሠረት ነው
Mar 1, 2026 121
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ የዓድዋ ድል ለአፍሪካዊያን የጋራ ደኅንነትና ወታደራዊ ትብብር ትልቅ መሠረት መሆኑን የኢፌዴሪ መከላከያ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሐመድ ገለጹ፡፡ ሁለተኛው የአፍሪካ መከላከያ ሚኒስትሮች ኮንፈረንስ "ከአኩሪ ታሪክ፣ ወደ ብሩህ አድማስ" በሚል መሪ ሀሳብ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል። በዚህ ኮንፈረንስ የአፍሪካ መከላከያ ሚኒስትሮች፣ ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች፣ ወታደራዊ አታሼዎችና ተመራማሪዎች እንዲሁም የጸጥታና ደኅንነት ተቋማት ኃላፊዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ። የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሐመድ በዚሁ ወቅት፤ የዓድዋ ድል የአፍሪካውያን የነፃነት ፋና ወጊ ከመሆኑ ባለፈ ለዛሬው አህጉራዊ ትብብር ዋነኛ መነሻ ነው፡፡ አፍሪካውያን በዓድዋ ድል የታየውን የይቻላል መንፈስ በመሰነቅ አህጉራዊ የጸጥታ እና ወታደራዊ ትብብራቸውን ይበልጥ ማጠናከር ይኖርባቸዋል ብለዋል። መድረኩ ነገ የካቲት 23 የሚከበረውን 130ኛውን የዓድዋ ድል በዓል ታሳቢ ያደረገ ሲሆን ድሉ ለጥቁር ሕዝቦች ኩራትና ለነፃነት ተጋድሎ መነሻ መሆኑ ተናግረዋል፡፡ የሁለትዮሽና አህጉራዊ ትብብር፡ የአፍሪካ አገራት አሁን ያለውን ተለዋዋጭና ውስብስብ የዓለም የፖለቲካና የጸጥታ ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባት ከመቼውም ጊዜ በላይ በጋራ ሊቆሙ ይገባል ብለዋል። ድሉ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ያለ ምንም ልዩነት በጋራ በመቆም ያሳኩት የቆራጥነትና የአልገዛም ባይነት ውጤት መሆኑን ጠቁመው ይህ አንድነት ዛሬም ለአፍሪካ ሰላምና ደኅንነት ዋስትና መሆኑን ገልጸዋል። የዓድዋ ድል በአፍሪካና በሌሎች ዓለማት የሚገኙ ሕዝቦች ለፍትሕ፣ ለእኩልነትና ለነፃነት እንዲታገሉ መንገድ የከፈተ ታሪካዊ ገድል መሆኑን አብራርተዋል። አገራቱ በትብብርና በጋራ ተጠቃሚነት መርህ ላይ በመመስረት የጋራ ትብብር አቅም መገንባት እንዳለባቸውም ገልዋጸል።
ብልፅግና ፓርቲ ዋና መገለጫው ለሕዝብ የገባውን ቃል በተግባር በመፈጸም ውጤት ማስመዝገብ ነው
Mar 1, 2026 109
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2018 (ኢዜአ)፦ብልፅግና ፓርቲ ዋና መገለጫው ለሕዝብ የገባውን ቃል በተግባር በመፈጸም ውጤት ማስመዝገብ ነው ሲሉ በፓርቲው የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መለሰ ዓለሙ ገለጹ። ፓርቲው በዘንድሮው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ላይ በንቃት ለመሳተፍ የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን እያከናወነ ይገኛል። 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሕዝብ ድምጽ አሸናፊ የሚሆንበት ለማድረግ በትኩረት እየሰራን ነው ከእነዚህ የዝግጅት ምዕራፎች መካከል አንዱ የሆነውን "ኢትዮጵያ ወደ ተምሳሌት ሀገር" በሚል መሪ ሀሳብ የተቀረጸውን ማኒፌስቶውን አስተዋውቋል። ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋር ቆይታ ያደረጉት የፓርቲው የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መለሰ ዓለሙ እንደተናገሩት፤ ማኒፌስቶው የተዋወቀበት መሪ ሀሳብ ፓርቲው የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ከፍታ ለማረጋገጥ ያለውን ፅኑ አቋም ያመለክታል። ይህም ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲ፣ በሰው ሀብት ልማት እና በኢኮኖሚ ሉዓላዊነት ያላትን የመሪነት ሚና ይበልጥ ለማጠናከር ዓላማ ያደረገ ነው ብለዋል። በዚህም መሠረት ፓርቲው ለሀገሪቷ የከፍታ ጉዞ ስኬት የነደፋቸውን ሀሳቦችና ፖሊሲዎች ለኢትዮጵያውያን ይፋ ማድረጉን ገልጸዋል። የፓርቲው አንዱ መገለጫ ብዝሃነት እና አካታችነት መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊው፤ ማኒፌስቶው በሁሉም መራጭ ዘንድ ተደራሽ እንዲሆን በተለያዩ ቋንቋዎች እንዲዘጋጅ መደረጉንም አክለዋል። አቶ መለሰ አያይዘውም ፓርቲው የዘንድሮውን ማኒፌስቶ ሲያስተዋውቅ፣ ካለፈው የምርጫ ወቅት ጀምሮ በተግባር ተፈትኖ ካስመዘገባቸው ተጨባጭ ስኬቶች በመነሳት እንደሆነ አመልክተዋል። በወቅቱ በማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ዘርፎች ለማከናወን ለሕዝብ ቃል የገባቸውን ጉዳዮች ከግብ ማድረስ መቻሉንም ጠቁመዋል። ይህ ስኬት ሊመዘገብ የቻለው ከሕዝብ ጋር በትብብርና በመደማመጥ እንዲሁም በጥብቅ የአመራር ክትትል በመሥራቱ መሆኑን አንስተዋል። ፓርቲው በስድስተኛው ጠቅላላ ምርጫ ለማከናወን ያቀዳቸውንና ቃል የገባቸውን ተግባራት በውጤታማነት ስለመፈጸማቸው በመስክ ጥናት እና በግምገማ ማረጋገጡን ገልጸዋል። ለዘንድሮው የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ፓርቲውን ወክለው የሚወዳደሩ ዕጩዎችን የመለየት ሥራ ኢትዮጵያን በሚመስል የአካታችነት መስፈርት መከናወኑን ተናግረዋል። የዕጩዎች ምዝገባ በዲጂታል ሥርዓት መካሄዱ ልዩ እንደሚያደርገው ጠቅሰው፤ ፓርቲው የምርጫ ቦርድን አሠራር ተከትሎ በመላ ሀገሪቷ ዕጩዎቹን ማስመዝገቡንም አብራርተዋል።
የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የአዘርባጃን ጉብኝት የሁለቱን ሃገራት ትብብር የሚያጠናክር ነው- ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር)
Feb 28, 2026 115
አዲስ አበባ፤ የካቲት 21/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ልኡካቸው በአዘርባጃን ያደረጉት የስራ ጉብኝት በሀገራቱ መካከል ያለውን ትብብር ዘላቂነት የበለጠ የሚያጎለብት መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአዘርባጃን ያደረጉትን የስራ ጉብኝት አስመልክቶ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በኢትዮጵያ እና አዘርባጃን መካከል ያለው የሁለትዮሽ ግንኙነት ባለፉት ዓመታት እየተጠናከረ እና የትብብር አድማሱ እየሰፋ እንደሚገኝ በማብራሪያቸው አመልክተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በመሪ ደረጃ በአዘርባጃን ጉብኝት ማድረጋቸው እና በተለያዩ መስኮች ስምምነት መፈረማቸው በሀገራቱ መካከል ያለውን የሁለትዮሽ ትብብር ዘርፈ ብዙና ቀጣይነት ያለው እንዲሆን ድርሻው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። ሀገራቱ በአዳዲስ ዘርፎች ትብብር ለመፍጠር የጋራ መግባባት ላይ መድረሳቸውንም አመልክተዋል። 29ኛውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የዓየር ንብረት ለውጥ ጉባኤ(ኮፕ 29) በተሳካ ሁኔታ ያስተናገደችው አዘርባጃን መሰል ዓለም አቀፍ መድረኮችን በማዘጋጀት ጥሩ ልምድ ያዳበረች መሆኑን ገልጸዋል። አዘርባጃን ይሄንን ልምድ ለማጋራትና አብሮ በትብብር ለመስራት ከፍተኛ ፍላጎትና ተነሳሽነት እንዳላት ማሳየቷንም ሚኒስትሩ ገልጸዋል። በሌላ በኩል አዘርባጃን ኢትዮጵያን የአፍሪካ መግቢያ በር አድርጋ እንደምታይና የኢንቨስትመንት እና የንግድ ተደራሽነቷን ለማስፋት እንደምትፈልግ መግለጿን ተናግረዋል። ሁለቱ ሀገራት የንግድ እና ኢንቨስትመንት ትብብራቸውን ለማጠናከር መስማማታቸውንም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ አዘርባጃን የህዝብ አገልግሎቷን በቴክኖሎጂ በመደገፍ እያከናወነች ያለው ውጤታማ ስራ ልምድ የምትቀስምበት እንደሆነም አንስተዋል። አጠቃላይ ጉብኝቱ ውጤታማ እንደነበረ እና ለቀጣይ ትብብር ምቹ መደላድል የፈጠረ መሆኑን ነው ሚኒስቴሩ ያነሱት።
ፓርቲዎች ማኒፌስቷቸውን ለህዝብ በማስተዋወቅ ምርጫን በሀሳብ የበላይነት ለማሸነፍ የጀመሩት ጥረት መጠናከር አለበት −ምሁራን
Feb 28, 2026 123
ዲላ፤ የካቲት 21/2018(ኢዜአ) ፡-የፖለቲካ ፓርቲዎች ማኒፌስቷቸውን ለህዝብ በማቅረብና በማስተዋወቅ ምርጫን በሀሳብ የበላይነት ለማሸነፍ የጀመሩት ጥረት የሚበረታታና መጠናከር ያለበት ነው ሲሉ የዲላ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ። ምርጫ ዴሞክራሲ የሚገነባበት ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው መስፈርት መሆኑን ያነሱት ምሁራኑ ውጤታማ ምርጫ በማካሄድ የሀገርን መልካም ስም ማስቀጠል እንደሚገባም ተናግረዋል። የዲላ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ኤልያስ ዓለሙ (ዶ/ር)፣ የውስጥ አቅምን በመጠቀም ውጤታማ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ምቹ የፖለቲከ ምህዳር በመንግስት ስለመፈጠሩ ጅማሬው እየታየ መሆኑን ገልጸዋል። ፓርቲዎች ማኒፌስቷቸውን ለህዝብ በማቅረብና በማስተዋወቅ ምርጫን በሃሳብ የበላይነት ለማሸነፍ የጀመሩት ጥረት የሚበረታታ መሆኑን አንስተው ይህም መጠናከር እንዳለበት አመልክተዋል። ምርጫ ዴሞክራሲን ከመገንባት ባለፈ የህዝብ ድምጽ እንዲደመጥ ያደረጋል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ በሰከነና የምርጫ ህጉን በተከተለ መልኩ የሚደረግ የሀሳብ ሙግትና ፉክክር የተሻለ የፖለቲካ ስርዓት በመገንባት ሀገርን ያጸናል ብለዋል። በመሆኑም ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች እና መራጩ ህዝብ የሃሳብ የበላይነትን ለድርድር ማቅረብ የለባቸውም ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ምርጫ የዲሞክራሲ ልምድ የሚገነባበት ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው መስፈርት መሆኑን ያነሱት ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የትምህርት ዘርፍ መምህርና ተመራማሪ ደረጄ ክፍሌ (ዶ/ር) ናቸው። በመጪው ግንቦት ወር የሚካሄደውን 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ውጤታማ በማድረግ የሃገርን መልካም ስም ለመገንባት ሁሉም የምርጫው ተዋናዮች በሃላፊነት ስሜት መንቀሳቀስ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች በተለያዩ የመገናኛ ብዙሀን ማኒፌስቶና ያሏቸውን አማራጮች ለህዝብ ለማስተዋወቅ የጀመሯቸውን ጥረቶች አጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ገልጸዋል። በተለይ ፓርቲዎች በሀሳብ የበላይነት ልቆ ለመውጣት ቅድሚያ መስጠት እንዳለባቸው ተናግረው በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ከግጭት ቀስቃሽ ንግግርና ተግባር መቆጠብ አለባቸው ብለዋል። በሀሳብ የበላይነት ምርጫን ለማሸነፍ የሚደረጉ ጥረቶች ዴሞክራሲ እንዲያብብ ሚናው የጎላ በመሆኑ ፓርቲዎችና አባላቶቻቸው በዚህ መልክ የጀመሩትን ጥረት ማጠናከር እንዳለባቸው አመልክተዋል።
የዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሴቶች በንቃት መሳተፍ ይጠበቅባቸዋል
Feb 28, 2026 122
ሰመራ፤ የካቲት 21/2018(ኢዜአ)፦ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሴቶች በንቃት መሳተፍ እንደሚጠበቅባቸው የኢትዮጵያ ሴቶች ፌዴሬሽን ገለፀ። ፌዴሬሽኑ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ታዛቢዎችን ለማሰማራት በአፋር ክልል ክላስተር ደረጃ የታዛቢዎች የአሰልጣኞች ስልጠና እየሰጠ ይገኛል። ስልጠናውን ያስጀመሩት የኢትዮጵያ ሴቶች ፌዴሬሽን ዋና ዳይሬክተር ገነት ስዩም እንደተናገሩት ሴቶች በዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ በንቃት በመሳተፍ ምርጫው ሰላማዊና ፍትሃዊ ሁኖ እንዲጠናቀቅ ሀላፊነታቸው መወጣት አለባቸው። ሴቷ ለመመረጥም ይሁን ለመምረጥ እንዲሁም በታዛቢነት ተሳትፎዋን ማሳደግ እንድትችል የአሰልጣኞች ስልጠናው ጉልህ ድርሻ እንዳለው ተናግረዋል። ላለፉት ዓመታት ምርጫዎችን በመታዘብና ግንዛቤ በመስጠት የተሳተፈው ፌዴሬሽኑ የሴቶችን ሁለንተናዊ ተሳታፊነትና ተጠቃሚነት በማሳደግ ረገድም ሰፋፊ ስራዎችን ሲሰራ መቆየቱን ገልፀዋል። የመራጮችን ግንዛቤ ከማሳደግ አንጻር በዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ በተለያዩ አማራጮች በመጠቀም የማህበረሰብ ክፍሎችን ተደራሽ ለማድረግ መታቀዱን ተናግረዋል። የአፋር ክልል ሴቶች ፌዴሬሽን ዳይሬክተር ፋጡማ ሐንፈሬ በበኩላቸው እየተሰጠ ያለው የአሰልጣኞች ስልጠና ቀጣዩ ምርጫ ሰላማዊ ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የሚያግዝ ነው።
ምርጫው ለዴሞክራሲ ስርዓት መጎልበትና ለሀገረ መንግስት ግንባታ ጥሩ መሰረት እንዲያኖር የፖለቲካ ፓርቲዎች መስራት ይገባቸዋል
Feb 28, 2026 104
መቱ፤ የካቲት 21/2018(ኢዜአ)፦ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለዴሞክራሲ ስርዓት መጎልበትና ለሀገረ መንግስት ግንባታ ጥሩ መሰረት እንዲያኖር የፖለቲካ ፓርቲዎች መስራት እንደሚገባቸው ምሁራን ገለጹ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚወዳደሩ የፖለቲካ ፓርቲዎችን የምርጫ ምልክት ይፋ ያደረገ ሲሆን የምርጫ ሂደቱም ነፃ፣ ሰላማዊና ፍትሃዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ፓርቲዎች የምርጫ ህጉን አክብረው እንዲሰሩ አስገንዝቧል። አጠቃላይ የምርጫ ሂደቱንና የፓርቲዎችን ሃላፊነት በተመለከተ ኢዜአ በመቱ ዩኒቨርሲቲ የሚሰሩ ምሁራንን አነጋግሯል። በዩኒቨርሲቲው የሕግ ትምህርት ቤት ዲን ዩሱፍ ጋዛሊ፤ የምርጫ ዴሞክራሲያዊነት መለኪያው ሂደቱና የፓርቲዎች ሰላማዊና ደሞክራሲያዊ እንቅስቃሴ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በቅድመ ምርጫ ፓርቲዎች የምርጫ ስነ ምግባር ደንቡን በማክበር የመወዳደሪያ ሐሳባቸውን ለሕዝብ በመሸጥ ተቀባይነት ለማግኘት መስራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። ፓርቲዎች የሃሳብና የፖሊሲ ክርክር ላይ ማተኮር እንዳለባቸውም ተናግረዋል። በምርጫው መሳተፍ ዴሞክራሲያዊ መብትና የዜግነት ኃላፊነት በመሆኑ በሂደቱ ለሀገር ሕልውናና ቀጣይነት ቅድሚያ ሰጥተው መስራት ግደታ እንዳለባቸውም አንስተዋል። በመሆኑም የዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ ለዴሞክራሲ ስርዓት መጎልበትና ለሀገረ መንግስት ግንባታ ጥሩ መሰረት አኑሮ እንዲያልፍ የፖለቲካ ፓርቲዎች መስራት ይገባቸዋል ነው ያሉት። በዩኒቨርሲቲው የሥነ-ባሕርይ እና ሥነ-ሰብ ኮሌጅ መምህር ወንዱ መብራቴ፤ በምርጫው የሚፎካከሩና የሚሳተፉ ሁሉ ከምንም በላይ የሀገርን ሰላምና ህልውና ጉዳይ ቅድሚያ መስጠት ግደታ አለባቸው ብለዋል። በምርጫው ሂደት ፓርቲዎች በሀሳብ የበላይነት ለመወዳደር ዝግጁ ሆነው አሸናፊ ሃሳብ ይዘው ሊመጡ እንደሚገባም ገልጸዋል። በመሆኑም ጠቅላላ ምርጫው ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊ፣ ፍትሐዊና ተአማኒ ሆኖ እንዲካሄድ የሚፎካከሩ ፓርቲዎችና ደጋፊዎች የየበኩላቸውን ኃላፊነት ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።
7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሕዝብ ድምጽ አሸናፊ የሚሆንበት ለማድረግ በትኩረት እየሰራን ነው - ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች
Feb 28, 2026 180
አዲስ አበባ፤ የካቲት 21/2018(ኢዜአ)፦ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሕዝብ ድምጽ አሸናፊ የሚሆንበትና የሕዝብ ፍላጎት የሚንጸባረቅበት እንዲሆን በትኩረት እየሰሩ መሆኑን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ገለጹ። 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ይፋ ያደረገው የጊዜ ሰሌዳ ያሳያል። ቦርዱ ምርጫውን ማካሄድ የሚያስችሉ የተለያዩ ቅድመ ዝግጅቶችን በማድረግ ላይ ሲሆን የመራጮች ምዝገባም ከየካቲት 28 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ያካሂዳል። ፓርቲዎችም ዕጩዎቻቸውን ያስመዘገቡ ሲሆን ምርጫ አስፈጻሚዎች የአሰልጣኞች ሥልጠናም በቦርዱ በኩል እየተሰጠ ይገኛል። በቅርቡ ቦርዱ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የሚሳተፉ የፖለቲካ ፓርቲዎችን የምርጫ ምልክት ይፋ ያደረገ ሲሆን የፖለቲካ ፓርቲዎች የዕጩዎች የሥነ ምግባር ደንብም አዘጋጅቷል። ምርጫውን ፍትሃዊ፣ ዲሞክራሲያዊና ተዓማኒ ለማድረግ ያለመውን የሥነ ምግባር ደንብ ፓርቲዎች ፈርመውታል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ያነጋገራቸው ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምርጫው የሕዝብ የሥልጣን ባለቤትነት የሚረጋገጥበት እንዲሆን እየሰሩ ነው። የአማራ ዲሞክራሲያዊ ኃይል ንቅናቄ ሊቀ መንበር ተስፋሁን ዓለምነህ፤ ፓርቲው በምርጫው የነቃ ተሳትፎ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ፓርቲው የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ በርካታ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው፤ ምርጫው የሕዝብ ፍላጎት የሚንጸባረቅበት፤ ሕዝብ አሸናፊ የሚሆንበት አካሄድ ተከትለን በምርጫው ለመሳተፍ ዝግጁ ነን ብለዋል። ምርጫው በሂደቱም፣ በውጤቱም ሰላማዊ፣ ዲሞክራሲያዊና ተዓማኒ መሆን ይኖርበታል ያሉት አቶ ተስፋሁን በዚህ ረገድ ፓርቲያቸው የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል። ፓርቲው በምርጫው መወዳደር የሚያስችለውንና አማራጭ ሀሳብ የያዘውን ፕሮግራም መቅረጹን ጠቅሰው በምርጫው ለዲሞክራሲ ሥርዓት መጎልበት የበኩሉን አሻራ ለማሳረፍ ተግቶ ይሰራል ብለዋል። የሲዳማ አንድነት ፓርቲ ሊቀ-መንበር ለማ ኦያቶ በበኩላቸው፤ ፓርቲው ዕጩዎቹን ማስመዝገቡንና ለፓርቲው አባላት የአቅም ግንባታ ሥልጠና መስጠቱን አስታውቀዋል። ምርጫው ሠላማዊና ዲሞክራሲያዊ በሆነ መልኩ እንዲካሄድ ፓርቲው የበኩሉን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን አስረድተዋል። የወለኔ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ሊቀ-መንበር ፈይሰል አብዲላዚዝ እንደገለጹት፤ ለምርጫው ስኬታማነት የቦርዱን እንዲሁም የሀገሪቱን ሕግ አክብሮ መንቀሳቀስ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። ፓርቲው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በቅርቡ ይፋ ያደረገውን የዕጩዎች የሥነ ምግባር ደንብ መፈረሙን ጨምረው ጠቁመዋል። ተፎካካሪ ፓርቲዎች መሰል የሥነ ምግባር መርሆዎችን በመከተልና በመተግበር ሀገራዊ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባም ጠቁመዋል።
የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ክርክራቸውን የሀገርን ልማትና የህዝብን አብሮነት ማዕከል ባደረገ መልኩ ማካሄድ አለባቸው
Feb 27, 2026 173
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦የተፎካካሪ ፖለቲካ ፓርቲዎች የርዕዮተዓለም የምርጫ ክርክራቸውን የሀገርን ልማትና ዕድገት፣ የህዝብን አብሮነት እና መስተጋብር ማዕከል ባደረገ መልኩ ማካሄድ እንደሚኖርባቸው አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ነው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በመጪው ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ይፋ ማድረጉ ይታወቃል። በምርጫው የሚሳተፉ የፖለቲካ ፓርቲዎችም በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን አማራጮች የመወዳደሪያ ምልክትና ማኒፌስቷቸውን ለህዝብ በማስተዋወቅ ላይ ናቸው። ኢትዮጵያውያንም በምርጫው ድምጽ መስጠት የሚችሉበትን ካርድ ለመውሰድና ይበጀኛል የሚሉትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ እየተጠባበቁ ይገኛሉ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎችም፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ለህዝብ የሚያቀርቧቸው የምርጫ ቅስቀሳና ክርክሮች ከስሜት ይልቅ ዕውቀትና ምክንያታዊነትን ያስቀደሙ ሊሆኑ እንደሚገባ ገልጸዋል። የፖለቲካ ፓርቲዎች በመገናኛ ብዙኅን በኩል በክርክሮች ላይ የሚያቀርቧቸው አማራጭ የፖሊሲ ሀሳቦችና በቀጣይም የምረጡኝ ቅስቀሳዎች ዜጎች ይበጀኛል ለሚሉት ፓርቲ ድምጽ ለመስጠት ግንዛቤ መፍጠር እንደሚያስችል ተናግረዋል። አቶ ከድር ሰኢድ እንደገለጹት፤ የፖለቲካ ፓርቲዎቹ የክርክር መድረኮቹ ለኢትዮጵያ ዘላቂ ልማትና ዕድገት አዋጭ የሆኑ ሃሳቦችን ያነገቡ የፖለቲካ ድርጅቶችን ለይቶ ድምጽ ለመስጠት ዕድል ፈጥሯል ብለዋል። በዘንድሮው ምርጫ ላይ ንቁ ተሳትፎ እያደረጉ የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሚያደርጉት ክርክር ወቅትም ህዝብን የሚመጥን በዕውቀት ላይ የተመሰረተ ሃሳቦችን ማቅረብ እንደሚጠበቅባቸው ገልጸዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወጣት ውበት ደጉ በበኩሏ፤ ምርጫ ዜጎች ይበጀኛል ለሚሉት የፖለቲካ ፓርቲ ድምጽ የሚሰጡበት የአንድ ሀገር የዴሞክራሲ ሥርዓት መገለጫ ነው ብላለች። የፖለቲካ ፓርቲዎች የምርጫ ክርክርም የሀገርን ልማትና ዕድገት፣ የህዝብን አብሮነትና ዘላቂ ሰላም ግንባታ ማዕከል ማድረግ እንደሚኖርበት ገልጸዋል። ህዝቡም በመገናኛ ብዙሃን የሚተላለፉ የምርጫ ወቅት የፖለቲካ ፓርቲዎችን ክርክርን በመከታተል ሀሳባቸውን ከብሄራዊ ጥቅም አኳያ መፈተሽ እንዳለበት አመልክተው፤ ለሀገራዊ ምርጫ ነፃ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊነት ገንቢ ሚና መወጣት እንዳለበት ተናግረዋል። አቶ አማን ማሞ በበኩላቸው፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች የክርክር መድረክ የህዝብን አንድነትና ሰላም ባከበረና በሃሳብ የበላይነት የተመሰረተ መሆን አለበት ብለዋል። ምርጫ የጠንካራ መንግስት ምስረታ፣ የሰላማዊ ፉክክርና የዴሞክራሲ ሥርዓት መገለጫ ነው ያሉት ደግሞ ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ ትዕግስት ማሞ ናቸው። በዚህም የፖለቲካ ፓርቲዎች በምርጫ ክርክር ወቅት ዕውቀትና የሀገርን ቀጣይነት የሚያስቀድሙ ሃሳቦችን ለህዝቡ በመሸጥ ለምርጫው ዴሞክራሲያዊነት በኃላፊነት መንፈስ መንቀሳቀስ እንዳለባቸው ገልጸዋል። መራጩ ህዝብም ለሀገርና ህዝብ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ይሰራል ይበጃል ለሚለው የፖለቲካ ፓርቲ ድምጽ ለመስጠት የሚችሉት የምርጫ ክርክሩንና የቅስቀሳ መርሃ ግብሩን ሲከታተሉ መሆኑን ነው የተናገሩት።
በብልጽግና ፓርቲ መሪነት ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ ስኬቶች ተመዝግበዋል
Feb 27, 2026 129
ሆሳዕና፤ የካቲት 20/2018(ኢዜአ)፦በብልጽግና ፓርቲ መሪነት ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የልማት ሥራዎች ህዝብን ተጠቃሚ ያደረጉ ስኬቶች መመዝገባቸውን የሀድያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቲዎስ አኒዮ ገለጹ። የብልጽግና ፓርቲ የህዝብን የልማት ጥያቄዎች ለመመለስ ባደረጋቸው ጥረቶች የተገኙ ስኬቶችን አጠናክሮ ያስቀጥላል በመጪው ግንቦት ወር የሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የዴሞክራሲ ምህዳርን በማጠናከር አዲሷን ኢትዮጵያን ለመገንባት ሚናው የጎላ መሆኑም ተመላክቷል። ብልጽግና ፓርቲ የዘንድሮ ጠቅላላ ምርጫ መወዳደሪያ ምልክቱ የሆነውን (የስንዴ ነዶ) እና ማኒፌስቶ ዛሬ በሆሳዕና ከተማ ለህዝብና ለአባላቱ አስተዋውቋል፡፡ የሀዲያ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማቲዎስ አኒዮ በዚህ ወቅት እንዳሉት ብልጽግና ፓርቲ በድህነት ቅነሳ ላይ ባከናወናቸው ተግባራት ተጨባጭ ውጤት ተመዝግቧል። ፓርቲው የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ሀሳቦችን በማቅረብና ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ጭምር በትብብር በመስራት ስኬት እያስመዘገበ መሆኑንም አስታውሰዋል፡፡ በዞኑ በሰላም ግንባታ፣ በገቢ አሰባሰብ፣ በሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በጤናና በትምህርት ዘርፍ በተከናወኑ ሥራዎች ተስፋ ሰጪ ወጤት እየተመዘገበ ስለመሆኑም ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከድህነት በመውጣት በምግብ ራስን ለመቻል በተተገበሩ የሌማት ትሩፋት መርሀግብርና ሌሎች ኢኒሼቲቮች ተጨባጭ ውጤት መምጣቱንም ጠቁመዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት በፓርቲው መሪነት በተለያዩ ዘርፎች በተከናወኑ የልማት ሥራዎች የህዝብን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ውጤቶች መመዝገባቸውንም ነው ያስታወቁት። በዞኑ በልማትና በመልካም አስተዳደር በተሰሩ ሥራዎች እየተመዘገቡ ያሉ ውጤቶች ተጠናክረው እንዲቀጥሉ የፓርቲው አመራሮችና አባላት የበኩላቸውን ሊወጡ ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል። በብልጽግና ፓርቲ የሀዲያ ዞን ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ታምራት ግዛው በበኩላቸው፤ የለውጡ መንግሥት የፖለቲካ ስልጣን ቅቡልነት በህዝብ ድምፅ ብቻ እንዲወሰን ማድረጉን ተናግረዋል፡፡ የዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ በሀገሪቱ የተጀመረውን የዴሞክራሲ ምህዳር በማጠናከር ለአዲሷ ኢትዮጵያ ግንባታ ሚናው ከፍተኛ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ በመርሃ ግብሩ ላይ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮችና የፓርቲው አባላት ተሳትፈዋል፡፡