ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
ለሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የምርጫ ማስፈጸሚያ ቁሳቁስ የማሟላትና የምርጫ ጣቢያዎችን ምቹ የማድረግ ሥራ ተከናውኗል
May 31, 2026 43
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ለሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የምርጫ ማስፈጸሚያ ቁሳቁስ የማሟላትና የምርጫ ጣቢያዎችን ምቹ የማድረግ ሥራ መከናወኑን በአዲስ አበባ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ የሚገኙ የምርጫ ጣቢያ አስተባባሪዎች ገለጹ። ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ሰኞ ከማለዳው12 ሰዓት ጀምሮ ይካሄዳል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምፅ ለመስጠት 54 ሚሊየን 57 ሺህ 861 መራጮች መመዝገባቸውን አስታውቋል። ኢዜአ በአዲስ አበባ ቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 በምርጫ ክልል ስር በሚገኙ ምርጫ ጣቢያዎች ላይ ቅኝት አድርጓል። የለገሀር ኮንዶሚኒየም ምርጫ ክልል 21 እና 22 አስተባባሪ ትብለጽ ንጉሴ ፤ ለሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ አስፈላጊ የምርጫ ቁሳቁስ ሥርጭት መደረጉን ገልጸዋል። በምርጫ ጣቢያው ድምፅ ለመስጠት የሚመጡ አቅመ ደካሞች፣ አካል ጉዳተኞችና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ለማስተናገድ ዝግጅት መጠናቀቁንም ገልጸዋል። ዜጎች ነገ በሚደረገው ጠቅላላ ምርጫ ላይ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ መብታቸውን በአግባቡ እንዲጠቀሙ አስገንዝበዋል። በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 10 ሜድሮክ ካርጎና አቪየሽን ሰርቪስ ምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ ምትኩ ፈርሻ በበኩላቸው፤ የምርጫ ማስፈጸሚያ ቁሳቁስ ተሟልቷል ብለዋል። መራጮችም ከጠዋቱ 12 ሰዓት ጀምሮ በየምርጫ ጣቢያው በመገኘት ይበጀኛል ለሚሉት ፓርቲ ድምፅ እንዲሰጡ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የምርጫ ቁሳቁሶችን በማሟላት መራጮችን እየተጠባበቅን ነው
May 31, 2026 52
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በአዲስ አበባ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ የሚገኙ ምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁሶችን በማሟላት ለነገው ምርጫ መራጮችን እየተጠባበቁ መሆናቸውን ገለጹ። በኢትዮጵያ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ ይታወቃል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምፅ ለመስጠት 54 ሚሊየን 57 ሺህ 861 መራጮች መመዝገባቸውን አስታውቋል። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድም መራጮች ወደ የምርጫ ጣቢያዎች ለመራጭነት ሲሄዱ ማንነታቸውን የሚገልፅ ማስረጃና የመራጭነት ካርድ መያዝ እንደሚጠበቅባቸው አስገንዝቧል። በተመሳሳይ በምርጫዬ መተግበሪያ ወይም በድረ ገፅ የተመዘገቡ ደግሞ የምርጫ ካርዱን ቅጅ በስልክ ወይም በታተመ ቅጂ ይዞ መቅረብም እንደሚኖርባቸው አስታውቋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎትም በአዲስ አበባ የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ምርጫ ክልል-20 የምርጫ ጣቢያዎችን እንቅስቃሴ በተመለከተ ቅኝት አድርጓል። በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ የሀሴት እንግዳ ማረፊያ ምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ ብሩክ አማን፤ በጣቢያው ለምርጫ አስፈላጊ የድምፅ መስጫ ወረቀት፣ ኮሮጆና ሌሎች ቁሳቁሶች መሟላታቸውን አስታውቀዋል። በክፍለ ከተማው የወረዳ-01 ደጓ እናት ምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ ሀና ዳምጤ በበኩላቸው፤ ሁሉም አይነት የህብረተሰብ ክፍሎች በተመቻቸ ቦታ መምረጥ የሚችሉበት ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። ለሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ አስፈላጊው ቁሳቁስና ግብዓቶችን በማሟላት መራጮች የሚጠለሉባቸው ማርፊያ ዳሶች ጭምር ተዘጋጅተዋል ያሉት ደግሞ የጀሞ አንድ ኮንዶሚኒየም ብሎክ 92 የምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ ታሪኩ ደርሶ ናቸው። የየምርጫ ጣብያ አስተባባሪዎቹ አያይዘውም ማህበረሰቡ ነገ ከጠዋቱ 12 ሰዓት ጀምሮ ወደ ምርጫ ጣቢያዎች በመምጣት ለሀገርና ለህዝብ ይበጃል የሚሉትን ፓርቲ እንዲመርጡ ጥሪ አቅርበዋል።
ለመምረጥ የድምፅ መስጫ ዕለቱን በጉጉት እየተጠባበቅን ነው
May 31, 2026 56
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ለመምረጥ ድምፅ መስጫ ዕለቷን በጉጉት እየተጠባበቁ መሆናቸውን በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚካሄድ ይታወቃል። በእለቱም 54 ሚሊየን 57 ሺህ 861 የምርጫ ካርድ የወሰዱ መራጮች ለሀገርና ለህዝብ ይጠቅማል ብለው ያመኑበትን አካል እንደሚመርጡ ይጠበቃል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎትም ነገ የሚካሄደውን ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ አስመልክቶ በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ምርጫ ክልል-19 ያለውን እንቅስቃሴ በተመለከተ ቅኝት አድርጓል። ነዋሪዎቹ እንዳሉት በነገው እለት በሚካሄደው ምርጫ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል መሰረት ረጋሳ እንዳለችው፤ የምርጫ ካርዷን አውጥታ ቀኑን በመጠባበቅ ላይ መሆኗን ተናግራለች። ሌላው ነዋሪ ሰኢድ አሊ በበኩላቸው፤ የምርጫ ካርዳቸውን በወቅቱ ወስደው ዝግጅት ሲያደርጉ መቆየታቸውን ገልጸው፤ ነገ በማለዳ በመውጣት የዜግነት ግዴታቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ እመቤት ፈይሳ እንደገለጸቸው፤ እንደዜጋ ለሀገር ዕድገትና ልማት ይበጃል የምለውን ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅቻለሁ ነው ያለችው። ሌላኛው ነዋሪ አስፋው አሰፋ በበኩላቸው፤ የምርጫውን ዕለት በጉጉት እየተጠባበቁ መሆናቸውን በመግለጽ በማለዳ በመውጣት ይበጀኛል ለሚሉት ፓርቲ ድምፃቸውን ለመስጠት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል።
በጋምቤላ ክልል ጎግ ወረዳ ምርጫ ክልል ነገ ለሚካሄደው ምርጫ የተደረገው ዝግጅት ሙሉ በሙሉ ተጠናቋል
May 31, 2026 85
ጎግ ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል በአኝዋሃ ዞን ጎግ ወረዳ ምርጫ ክልል በነገው ዕለት ከማለዳ ጀምሮ ለሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ የተሟላ ዝግጅት መደረጉ ተገለፀ። የምርጫ ክልሉ አስተባባሪ አቶ ንብረት ሰውየው ለኢዜአ አንደገለፁት በምርጫ ክልሉ በሚገኙ በሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች በነገው እለት ለሚካሄደው ምርጫ የቁሳቁስ ስርጭት በተሟላ ሁኔታ መደረጉን ነው የገለፁት። የምርጫ ታዛቢዎችም በየምርጫ ጣቢያው በሰዓቱ በመገኘት ሂደቱን ለመታዘብ ዝግጁ መሆናቸውንም አብራርተዋል። በወረዳው የምርጫ ክልል 19 የምርጫ ጣቢያዎች መኖራቸውን ጠቁመዋል።
የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀመንበር እና ኡሁሩ ኬንያታ በምርጫ ታዛቢ ቡድኖች ዝግጅት ዙሪያ ተወያዩ
May 31, 2026 90
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀመንበር አምባሳደር ሰልማ ማሊካ ሃዳዲ፣ ከአፍሪካ ህብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪ ከሆኑት ከኡሁሩ ኬንያታ ጋር ውይይት አድርገዋል። ውይይቱ ስለ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ቅድመ-ዝግጅቶች እና ታዛቢ ቡድኖች ግልጽና ዲሞክራሲያዊ ሂደቶችን በመደገፍ ረገድ ያላቸው ሚና ላይ ያተኮረ ነው። በተጨማሪም በአፍሪካ ህብረት የተለያዩ ተልዕኮዎች ዙሪያም ሀሳቦችን መለዋወጣቸውን የህብረቱ መረጃ ያመለክታል።
የባህርዳር ምርጫ ክልል ምርጫ ጣቢያዎች ለሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል
May 31, 2026 105
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የባህርዳር ምርጫ ክልል ምርጫ ጣቢያዎች ለሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል። ኢትዮጵያ ነገ ሰባተኛውን ጠቅላላ ምርጫ ታካሂዳለች። ኢዜአ በባሕርዳር የምርጫ ክልል የተለያዩ ምርጫ ጣቢያዎች ተንቀሳቅሶ የዝግጅት ሥራዎች ምን እንደሚመስሉ ቃኝቷል። የምርጫ ጣቢያዎቹ አስተባባሪዎች እንደገለፁት ከትናንን ጀምሮ የምርጫ ቁሳቁስን ወደ ጣቢያ የማሰራጨት፣ ለምርጫው አስፈላጊ መሠረተ ልማቶችን የማሟላት ሥራዎች በተሳካ ሁኔታ መከናወናቸውን ገልጸዋል። በፋሲሎ ክፍለ ከተማ 15/1ሀ ምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ ሄለን ዓለሙ፥ የመራጮች ድምፅ መስጫ ኮሮጆና ሌሎችም ቁሳቁሶችን ተረክበው ማዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ለመራጮች የድምፅ አሰጣጥ ሂደት ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የድንኳን ተከላና ወንበሮች በበቂ ሁኔታ መዘጋጀታቸውን ጠቅሰዋል። በግሽ ዓባይ ክፍለ ከተማ የ02/1 ምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ ፍስሐ ገረመው፥ የጣቢያው ምርጫ አስፈጻሚዎችና የቁሳቁስ ዝግጅት ሙሉ ለሙሉ መጠናቀቁን ተናግረዋል። በዳግማዊ ምኒልክ ክፍለ ከተማ የአንድ በአንድ ምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ አዘዘው ጠገናው፥ በጣቢያው 1 ሺህ 500 መራጮች ድምፅ ለመስጠት መመዝገባቸውን ተናግረዋል። በነገው ዕለት ለሚካሄደው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ እንደ ጣቢያ የተሟላ የምርጫ ቁሳቁስ ዝግጅት መደረጉን አንስተዋል። የምርጫ ጣቢያ አስተባባሪዎቹ አክለውም ነገ ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ መራጮች ድምፅ መስጠት እንደሚጀምሩ ተናግረዋል። በየምርጫ ጣቢያው ታዛቢዎች በተገኙበት የምርጫ ሂደቱን ለማስፈጸም የተሟላ ዝግጅት ማድረጋቸውን አረጋግጠዋል።
በአርባ ምንጭ ምርጫ ክልል ሥር ባሉ የምርጫ ጣቢያዎች ለምርጫው ዝግጅቶች ተጠናቀዋል
May 31, 2026 96
አርባ ምንጭ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በአርባ ምንጭ ምርጫ ክልል ሥር በሚገኙ 227 የምርጫ ጣቢያዎች በነገው እለት ለሚካሄደው ምርጫ የዝግጅት ሥራዎች መጠናቀቃቸው ተገለጸ። ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ ምርጫ ጣቢያ ሃላፊዎች እንደገለጹት አስፈላጊውን ዝግጅት በማድረግ ጣቢያዎቹ ለነገ የድምጽ አሰጣጥ ሂደት ዝግጁ ተደርገዋል። በአርባ ምንጭ ከተማ የጫሞ ካምፓስ ምርጫ ጣቢያ ሃላፊ ሰለሞን ሳዳማ ለምርጫው ስኬታማነት አስፈላጊውን የዝግጅት ሥራ ማጠናቀቃቸውን ገልጸዋል፡፡ በዝግጅት ሥራው ድንኳን ተከላና አጠቃላይ የምርጫ ቁሶች በተሟላ ሁኔታ የማዘጋጀት ሥራ መከናወኑን ጠቁመዋል። ሌላኛዋ በከተማው የየትነበርሽ ወፍጮ ቤት ምርጫ ጣቢያ ሃላፊ መሠረት በቀለ ከምርጫ ቦርድ የመጡ ቁሶችን መረከባቸውን ጠቅሰው ለድምጽ አሰጣጥ ሂደት አስፈላጊውን ዝግጅት አድርገናል ብለዋል። የምርጫ ሃላፊ፣ የመዝገብ ሹምና ታዛቢዎች የሚቀመጡበት ስፍራ መዘጋጀቱንም ተናግረዋል፡፡ ለነገው የድምጽ አሰጣጥ ሂደት የሚያስፈልጉ ቁሶች ዝግጁ ናቸው ያሉት ደግሞ የአኩኩሉ ምርጫ ጣቢያ ሃላፊ አቶ እንዳልካቸው ምናሉ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል።
በሻሸመኔ ከተማ በሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ዝግጅት በተሟላ ሁኔታ ተጠናቋል
May 31, 2026 90
ሻሸመኔ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በሻሸመኔ ከተማ በሚገኙ ምርጫ ጣቢያዎች ነገ ለሚካሄደው የድምፅ አሰጣጥ ሂደት የምርጫ ዝግጅቱ በተሟላ ሁኔታ መጠናቀቁ ተገለፀ። የሻሸመኔ አንድ ምርጫ ክልል ኃላፊ አቶ አማረ ተክልዬ እንደገለፁት በምርጫ ክልሉ በሚገኙ 145 ምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁስ ስርጭትና ሌሎች ዝግጅቶች ተጠናቀዋል። በነገው ዕለት የድምፅ አሰጣጥ ሂደቱን ለማስጀመር የሚያስችል ሙሉ ዝግጅት በሁሉም ጣቢያዎች ላይ ተደርጓል ብለዋል። በምርጫ ክልሉ የአዋሾ አጂፕ ምርጫ ጣቢያ ታዛቢ የሆኑት ወይዘሮ መዲና በሪሶ በጣቢያው የምርጫ ቁሳቁስ በትናንትናው ዕለት ገብቶ መጠናቀቁን ገልፀዋል። በዛሬው ዕለትም ድንኳኖችን የማዘጋጀትና የተከላ ሥራ ተከናውኖ መጠናቀቁን ተናግረዋል። የሻላ ጀርባ ምርጫ ጣቢያ ታዛቢ የሆኑት አቶ መሀመድ ጩራ ለድምፅ አሰጣጥ ሂደቱ የሚያስፈልጉ ቁሳቁስ ሁሉም መግባታቸውን መመልከታቸውን ገልፀዋል። ለምርጫ አስፈፃሚዎችና ታዛቢዎች የሚሆኑ ቦታዎችና ቁሳቁስ ዝግጁ መደረጋቸውንም ጠቅሰዋል። መራጮች ለዝናብም ሆነ ለፀሐይ እንዳይጋለጡ የድንኳን ተከላ እንዲሁም ወንበር የማዘጋጀት ሥራም ተከናውኗል ብለዋል።
በሲዳማ ክልል የቱላ እና ጉጉማ የምርጫ ክልሎች ለነገው ጠቅላላ ምርጫ ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል
May 31, 2026 101
ውጅግራ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል የቱላ እና ጉጉማ ምርጫ ክልሎች ነገ ከማለዳው ጀምሮ ለሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን ገለጹ። የቱላ ምርጫ ክልል አስተባባሪ አቶ ምንተስኖት ስምኦን እንደገለጹት በምርጫ ክልሉ የሚገኙ 156 የምርጫ ጣቢያዎች የቁሳቁስ ስርጭት ተደርጓል። ጣቢያዎቹ በነገው ዕለት ከማለዳው ጀምሮ ለሚካሔደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ አስፈላጊውን ዝግጅት ማጠናቀቃቸውን ተናግረዋል፡፡ በምርጫ ክልሎቹ ከቦርዱ የተሰጡ ተግባራትን የሚያሳልጡ አስፈጻሚዎች ስምሪት ወስደው ስራ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። የጉጉማ ምርጫ ክልል አስፈጻሚ አቶ ደረጀ ደንግሶ በበኩላቸው በምርጫ ክልሉ በሚገኙ 78 የምርጫ ጣቢያዎች የቁሳቁስ ስርጭት፣ የድንኳን ተከላና ሌሎች የቅድመ ዝግጅት ተግባራት ተጠናቀው የድምጽ አሰጣጡን እየተጠባበቁ ይገኛሉ ብለዋል። በምርጫ ጣቢያዎቹ አስፈጻሚዎች ስምሪት ወስደው በስራ ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል።
በደሴ ከተማ ምርጫ ክልል ሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች ለነገው ምርጫ ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል
May 31, 2026 93
ደሴ ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ በደሴ ከተማ ምርጫ ክልል ሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች ለነገው ምርጫ ዝግጁ መሆናቸውን የምርጫ ጣቢያ አስተባባሪዎች ገለጹ። በደሴ ከተማ ምርጫ ክልል የአገር ግዛት ምርጫ ጣቢያ "ሀ" እና "ለ" አስተባባሪ አቶ አራጋው ተስፉ፣ በነገው እለት ለሚካሄደው ምርጫ የምርጫ ጣቢያዎቹ የተሟላ ዝግጅት ማድረጋቸውን ገልጸዋል። የሆጤ ምርጫ ጣቢያ "ለ" አስተባባሪ አቶ ማስረሻ ጥላሁን እና ሌላኛዋ አስተባባሪ ወይዘሮ የምስራች መኮንን፤ ለምርጫው ዝግጅቱ ተሟልቶ ነገን እየጠበቅን እንገኛለን ብለዋል። በደሴ ከተማ አስተዳደር በሚገኙ 110 የምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁስ ተሟልቶ ለነገው ምርጫ ዝግጁ መሆናቸው ታውቋል። በመሆኑም መራጮች የምርጫ ካርዳቸውን በመያዝ ከማለዳው 12 ሰአት ጀምሮ ድምፃቸውን ለመስጠት ተዘጋጅተው እንዲመጡ አስተባባሪዎቹ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል።
በምርጫ ክልሎቹ ሥር ባሉ ምርጫ ጣቢያዎች ምርጫ ለማስፈፀም አስፈላጊው ዝግጅት ተጠናቋል
May 31, 2026 99
ወላይታ ሶዶ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በወላይታ ሶዶ ከተማ ሶዶ ዙሪያ ቁጥር-1 እና ሶዶ ዙሪያ ቁጥር-2 ምርጫ ክልሎች በሚገኙ ምርጫ ጣቢያዎች ምርጫ ለማስፈፀም አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን የምርጫ ጣቢያ ሃላፊዎች ተናገሩ። ለነገው ጠቅላላ ምርጫ በጣቢያዎቹ የምርጫ ቁሳቁስን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ ዝግጅቶችን በተመለከተ የኢዜአ ሪፖርተር የጣቢያዎቹን ኃላፊዎች አነጋግሯል። የምርጫ ጣቢያ ሃላፊዎቹ እንደገለጹት የድምፅ መስጫ ቁሶችን በመረከብ የነገውን ምርጫ ለማስፈፀም የዝግጅት ሥራ አጠናቀዋል። ከጣቢያ ኃላፊዎቹ መካከል በወላይታ ሶዶ ከተማ ሶዶ ዙሪያ አንድ ምርጫ ክልል ኪዳነምህረት ቀበሌ አሜን ሥጋ ቤት መንደር ምርጫ ጣቢያ ሃላፊ አቶ እንድሪያስ ዋትሮ እንደገለጹት፣ የድምፅ መስጫ ቁሶችን በወቅቱ በመረከብ ምርጫ ለማስፈጸም የሚያስችል ዝግጅት አድርገዋል። በጣቢያው ምርጫ ማስፈፀም የሚያስችሉ ግብአቶች እንዲሁም የሰው ሃይል ተሟልቶ በነገው እለት ለመራጮች ቀልጣፋ መስተንግዶ ለመስጠት የተሟላ ዝግጅት መደረጉንም አመልክተዋል። በሶዶ ዙሪያ ሁለት ምርጫ ክልል የብሩህ ተስፋ ስቴዲየም ዕድር መንደር ምርጫ ጣቢያ ኃላፊ አክሊሉ ኢጃጆ እና የግሪንላድ ሆቴል ምርጫ ጣቢያ ኃላፊ ብሩክ ምልኪያስ በበኩላቸው ለነገው ጠቅላላ ምርጫ አስፈላጊ ዝግጅት መጠናቀቁን ተናግረዋል። በምርጫ ጣቢያቸው ምርጫ ማከናወን የሚያስፈልጉ ቁሳቁስ ከመረከብ ባለፈ አስፈላጊ ዝግጅቶች ተደርገው ለነገ መራጮችን በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል።
የኢጋድ እና የአፍሪካ ህብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪዎች በአዲስ አበባ የቅድመ ምርጫ ምልከታዎችንና የትብብር ስራዎችን አስመልክቶ የጋራ ውይይት አደረጉ
May 31, 2026 125
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ የኢጋድ እና የአፍሪካ ህብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪዎች በአዲስ አበባ የቅድመ ምርጫ ምልከታዎችንና የትብብር ስራዎችን አስመልክቶ የጋራ ውይይት አድርገዋል። የኢጋድ የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪ ዶክተር ስፔሲዮዛ ዋንዲራ ካዚብዌ፣ ከቀድሞ የኬንያ ፕሬዝዳንት እና የአፍሪካ ህብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪ ከሆኑት ኡሁሩ ኬንያታ ጋር ዛሬ በአዲስ አበባ መክረዋል። የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪዎቹ ያደረጉት ውይይት ከምርጫው በፊት የተደረጉ ምልከታዎችን ለመለዋወጥና የታዛቢዎችን የስምሪት እቅድ ለመገምገም የሚያስችል መሆኑ ተገልጿል። በተጨማሪም በኢትዮጵያ ሰላማዊ፣ ግልጽ እና ሁሉንም ያካተተ የምርጫ ሂደት እንዲኖር የጋራ ቁርጠኝነታቸውንም አረጋግጠዋል። ዶክተር ስፔሲዮዛ እና ኡሁሩ ኬንያታ በየራሳቸው የልዑካን ቡድኖች መካከል ሊኖር ስለሚገባው የቅንጅት አሰራር በሰፊው መክረዋል። ሁለቱ የታዛቢ ቡድኖች የምርጫውን ሂደት አስመልክቶ የሚያዘጋጁትን የመጀመሪያ ደረጃ የምርጫ ሪፖርት ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በጋራ ለመግለጽ የጊዜ ሰሌዳ ማውጣታቸውንም ኢዜአ ከኢጋድ ሴክሬተሪያት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።
የባህርዳር ከተማ ነዋሪዎች ለመምረጥ ነገን በጉጉት እየተጠባበቁ ይገኛሉ
May 31, 2026 56
ባህርዳር ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ ካርዳቸውን በመጠቀም ለመምረጥ ነገን በጉጉት እየተጠባበቁ መሆናቸውን በባህርዳር ከተማ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለፁ። ከከተማዋ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ማህሌት በላይ በ7ተኛው ጠቅላላ ምርጫ በንቃት ለመሳተፍ የሚያስችላቸውን የምርጫ ካርድ ቀደም ሲል መውሰዳቸውን አውስተዋል። በወሰዱት የምርጫ ካርድም የተጀመረውን ልማትና ዕድገት ያፋጥናል ብለው ያመኑበትን ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅተው ዕለቱን በጉጉት እየጠበቁ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላኛው የከተማው ነዋሪ ሀጂ አዲስ አብዱራህማን እንዳሉት ያለፉትን ሁሉንም ምርጫዎች በንቃት በመሳተፍ ይመራኛል የሚሉትን ፓርቲ መምረጣቸውን አስታውሰዋል። በነገው እለት በሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫም በድምጻቸው የሚያምኑበትን ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ''በወሰድኩት የምርጫ ካርድ ዴሞክራሲያዊ መብቴን ተጠቅሜ ሀገር ይመራል፣ ያስተዳድራል ብዬ ያመንኩበትን ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅቻለሁ'' ያለው ደግሞ ወጣት ዘለዓለም አሸናፊ ነው። ''የወሰድኩትን ካርድ ይበጀኛል የምለውን ፓርቲ ለመምረጥ ነገን በጉጉት እየተጠባበኩ እገኛለሁ'' ብሏል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል።
ድምፃችን ዋጋ እንዳለው በመገንዘብ ነገን በጉጉት እየተጠባበቅን ነው- የአዲስ አበባ ነዋሪዎች
May 31, 2026 58
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ድምፃቸው ዋጋ እንዳለው በመገንዘብ በነገው ዕለት ለሀገርና ለህዝብ ይጠቅማል ብለው ያሰቡትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለፁ። ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ሰኞ ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ ይካሄዳል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምፅ ለመስጠት 54 ሚሊየን 57 ሺህ 861 መራጮች መመዝገባቸውን አስታውቋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የመዲናዋ ነዋሪዎች ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በካርዳቸው ነገን መወሰን የሚችሉበት በመሆኑ እለቱን በጉጉት እየተጠባበቁ ይገኛሉ። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል አባገዳ ሰይፉ ከድር እንዳሉት ምርጫ የሚበጀንን መንግሥት ለመወሰን የሚያስችል በመሆኑ ዲሞክራሲያዊና ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን ለመወጣት ተዘጋጅተዋል። ሌላዋ አስተያየት ሰጪ ስንታየሁ ረና በበኩላቸው ድምፃቸው ዋጋ እንዳለው በመገንዘብ በነገው እለት ለመጪው ትውልድ የተሻለ የሚሰራ መንግሥትን ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ምርጫ በአምስት ዓመት አንዴ የሚገኝ ክስተት መሆኑን በመግለጽ፤ በድምፃችን መንግሥት የሚሆነንን የምንወስንበት ነው ያሉት ጥዑመልሳን አብርሃም በበኩላቸው ድምፃቸውን ለመስጠት ዝግጅታቸውን አጠናቀው ዕለቷን እየተጠባበቁ መሆናቸውን ገልፀዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ኤልሳቤት ተፈራ፣ ሀሩን ንጉሴና አሚና ከማል በተለይ ወጣቱ ምርጫ የነገ መንግሥትን ለመመስረት የሚያስችል እድል መሆኑን በመገንዘብ ለስኬታማነቱ የበኩሉን ሊወጣ ይገባል ብለዋል።
በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ለትውልዱ የሚበጅን ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅተናል
May 31, 2026 75
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የሀገርን አንድነት በማስጠበቅ ለትውልዱ የሚበጅን ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ። ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ሰኞ ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ ይካሄዳል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምፅ ለመስጠት 54 ሚሊየን 57 ሺህ 861 መራጮች መመዝገባቸውን አስታውቋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች እንዳሉት፤ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የሀገርን አንድነት በማስቀጠል ለትውልድ የሚበጅ ፓርቲን ለመምረጥ ዝግጁ ናቸው። የመዲናዋ ነዋሪ ጌታቸው ረጋሳ፤ የሀገርን አንድነት በማስቀጠል ለነገው ትውልድ ይበጃል የሚሉትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። በዚህም በነገው ዕለት ምርጫ በሚጀመርበት ከጠዋቱ 12 ሰዓት ተገኝተው ለመምረጥ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያዊያንም የመራጭነት ካርዳቸውን በመጠቀም በማለዳ በመውጣት በድምፅ አሰጣጥ ሂደቱ ንቁ ተሳትፎ ማድረግ እንደሚኖርባቸው ጥሪ አቅርበዋል። ወጣት አብርሃም ለማ በበኩሉ፤ የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ያረጋግጣል ብሎ የሚያስበውን ፓርቲ በጠዋት ተነስቶ ለመምረጥ መዘጋጀቱን አረጋግጧል። ወይዘሮ በለጡ መኩሪያ፤ በነገው እለት በሰዓቱ በመገኘት ለመምረጥ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸው፤ ሌሎች ኢትዮጵያዊያንም የመምረጥ መብታቸውን መጠቀም እንዳለባቸው መክረዋል። በአዲስ አበባ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚካሄደው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የምርጫ ማስፈጸሚያ ቁሳቁሶች በየምርጫ ጣቢያዎች በመሰራጨት ዝግጁ እየሆኑ ይገኛሉ። በአዲስ አበባ የምርጫ ክልል-16 የምርጫ ጣቢያ ኃላፊ ጌታቸው መኩሪያ፤ በምርጫ ጣቢያው የተመዘገቡ መራጮችን በሰዓቱ ማስተናገድ የሚያስችል የምርጫ ቁሳቁስ ዝግጅት መጠናቀቁን አረጋግጠዋል። በነገው ዕለት ከጠዋቱ 12 ሰዓት የድምፅ አሰጣጥ ሥነ-ስርዓቱን ለማስጀመር ዝግጁ ነን ብለዋል።
በደገሀቡር ከተማ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በስኬት እንዲጠናቀቅ የፀጥታ ዝግጅት ተደርጓል
May 31, 2026 85
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በደገሀቡር ከተማ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በስኬት እንዲጠናቀቅ አስፈላጊው የፀጥታ ዝግጅት መደረጉን የሶማሌ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ልዩ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ረዳት ኮሚሽነር አደም ኢብራሂም ገለጹ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መርሀግብር መሰረትም ለምርጫው አስፈላጊ ዝግጅቶች ሲደረጉ ቆይተው የድምጽ መስጫ ቁሳቁሶች በየምርጫ ጣቢያዎች ተሰራጭተዋል። በሶማሌ ክልል ደገሀቡር ከተማ አስተዳደር በሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎችም የምርጫ ቁሳቁስ ወደ ምርጫ ጣቢያዎች መሰራጨቱ ነው የተነገረው። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የሶማሌ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ልዩ ጽህፈት ቤት ሀላፊ ረዳት ኮሚሽነር አደም ኢብራሂም ፤ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ በስኬት እንዲጠናቀቅ የፀጥታ አካላት ዝግጅት ማድረጋቸውን ተናግረዋል። የዝግጅት ስራዎችም ቀደም ብለው መከናወናቸውን ተናግረዋል። ፖሊስ በቁሳቁስ ስርጭት ወቅት እጀባ በማድረግ በየምርጫ ጣቢያዎችም በቂ ጥበቃ በመመደብ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በነገው እለት ለሚካሄደው ምርጫ አስፈላጊው የፀጥታ ስራ ዝግጅት መጠናቀቁንም ጠቁመዋል።
በደንዲ ሁለት የምርጫ ክልል ለሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች የድምጽ መስጫ ቁሳቁሶች ተሰራጭተዋል
May 31, 2026 73
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በደንዲ ሁለት የምርጫ ክልል ለሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች የድምጽ መስጫ ቁሳቁሶች መሰራጨታቸውን የምርጫ ክልሉ ኃላፊ አቶ ኢቲቻ ለታ ገለጹ። ለምርጫ ጣቢያዎች አስፈላጊ የሆኑት ግብዓቶች የድምጽ መስጫ ወረቀቶች፣ የመራጮች መዝገብ ፣ የድምጽ መስጫ ኮሮጆና የተለያዩ ቁሳቁሶች መሰራጨታቸውን ገልፀዋል። የቁሳቁስ ስርጭቱ በጥንቃቄና ደህንነቱ በተጠበቀ መልኩ እየተከናወነ ወደ ምርጫ ጣቢያዎች ተደራሽ መደረጉን ጠቁመዋል። የምርጫ ቁሳቁሶቹ በአግባቡ በምርጫ ጣቢያዎች መድረሳቸውን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ የምርጫ ታሪክ በርካታ መራጮች በተመዘገቡበት ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ሰኞ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ድምጽ ይሰጣል።
የጊንጪ ከተማ ነዋሪዎች ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ለመጠቀም ተዘጋጅተዋል
May 31, 2026 108
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦ነገ ማለዳ በምርጫ ጣቢያ ተገኝተው ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ለመጠቀም መዘጋጀታቸውን በምዕራብ ሸዋ ዞን የጊንጪ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። አስተያየታቸውን የሰጡት የከተማዋ ነዋሪዎች እንዳሉት፤ ይበጀናል ለሚሉት ድምጽ ለመስጠት በጉጉት በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ በዚህም መሠረት ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ለመጠቀምና የሚፈልጉትን ፓርቲ ለመምረጥ ዝግጅታቸውን አጠናቀዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከልም አቶ ቤለማ አብዶ እንዳሉት በማለዳ ተነስተው ድምጻቸውን ለሚፈልጉት ፓርቲ ለመስጠት ዝግጅት ማድረጋቸውን ተናግረዋል፡፡ ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ገላና ዲንቃ በበኩላቸው ምርጫ የዜጎች የዴሞክራሲ ተሳትፎ መሆኑን ገልጸው ነገ በማለዳ ተነስተው ድምፅ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን ጠቅሰዋል፡፡ በምርጫው ለሀገር ይጠቅማል ያሉትን ፓርቲ ለመምረጥ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ነገ በማለዳው ካርድ ባወጣንበት የምርጫ ጣቢያ ተገኝተን ለመምረጥ ተዘጋጅተናል ያሉት ደግሞ አቶ ምትኩ ቤኩማ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል። ቦርዱ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምፅ ለመስጠት 54 ሚሊየን 57 ሺህ 861 መራጮች መመዝገባቸውንም አስታውቋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሌሞ 01 ምርጫ ክልል ምርጫ ለማስፈጸም አስፈላጊው ዝግጅት ተጠናቋል
May 31, 2026 109
ሆሳዕና፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሀዲያ ዞን ሌሞ - 01 ምርጫ ክልል በሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች ምርጫ ለማስፈጸም አስፈላጊው ዝግጅት መጠናቀቁ ተገለጸ። የምርጫ ክልሉ ሀላፊ አቶ ሙሉቀን አሻግሬ እንደገለፁት በምርጫ ክልሉ ለሚገኙ 140 የምርጫ ጣቢያዎች የድምፅ መስጫ ቁሳቁስ ተሰራጭቷል። የምርጫ ቁሶቹ ደህንነታቸው በተጠበቀ መልኩ ወደሁሉም ምርጫ ጣቢያዎች እንደተላኩና በምርጫ ጣቢያዎች እንደደረሱ መረጋገጡንም ተናግረዋል።፡ በሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ሂደቱን ስኬታማ በሆነ መንገድ ለማከናወን የሚያስችል የዝግጅት ሥራ መጠናቀቁንም አስታውቀዋል። በምርጫ ክልሉ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አማካኝነት ስልጠና የወሰዱ የምርጫ ጣቢያ አስፈፃሚዎች ለነገው ምርጫ መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል። መራጮችም ነገ ከጠዋቱ 12 ሰዓት ጀምሮ በምርጫ ጣቢያዎቹ ተገኝተው ድምጻቸውን እንዲሰጡ በጣቢያዎቹ አስፈላጊው ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል። በሌሞ - 01 ምርጫ ክልል ሥር የሚገኘው ሆሳዕና ሄጦ ቀበሌ ጥምቀተ ባህር ፊት ለፊት ምርጫ ጣቢያ ምርጫ አስፈፃሚ አለምፀሐይ ቦጋለ፣ በነገው እለት ለሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ አስፈላጊው የምርጫ ቁሳቁስ ወደ ምርጫ ጣቢያው ደርሶ የዝግጅት ሥራው መጠናቀቁን አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል።
በወልቂጤ ምርጫ ክልል ለጠቅላላ ምርጫው ሲደረግ የነበረው ዝግጅት ተጠናቋል
May 31, 2026 93
ወልቂጤ ፤ ግንቦት 23/2018 (ኢዜአ)፦በማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የወልቂጤ ምርጫ ክልል ለጠቅላላ ምርጫው ሲደረግ የነበረው ዝግጅት መጠናቀቁን የምርጫ ክልሉ አስተባባሪ አቶ ሲሳይ ጀማል ገለጹ። የምርጫ ክልሉ አስተባባሪ አቶ ሲሳይ ጀማል፤ በሁሉም ምርጫ ጣቢያዎች የምርጫ ቁሳቁስ ሙሉ በሙሉ ተደራሽ መሆኑን ገልጸዋል። በምርጫ ክልሉ በሚገኙ 141 የምርጫ ጣቢያዎች ድምጽ ለመስጠት የሚያስችሉ ግብዓቶች ተሟልተው ድምጽ ለመስጠት ዝግጁ መሆናቸውን ጠቁመዋል። የውሃ ልማት ሰፈር ምርጫ ጣቢያ ኃላፊ አቶ መኖር ግርማ፤ በምርጫ ጣቢያው የድምጽ አሰጣጡን ሂደት ስኬታማ ለማድረግ የሚያስችል አስፈላጊው ዝግጅት መጠናቀቁን ገልጸዋል። በጣቢያው የሚያስፈልጉ የድምጽ መስጫ ቁሳቁሶች ተጠቃለው መድረሳቸውን ጠቅሰው፣ በነገው እለት ለመራጩ አመቺ በሆነ ቦታ ላይ የድምጽ መስጫ ድንኳኖችና መቀመጫ ወንበሮች መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። የእድገት በር ቦሎ መንደር ኪራይ ቤት ምርጫ ጣቢያ አስተባባሪ ወይዘሮ አለም ደስታ በበኩላቸው፤ ምርጫ ጣቢያዎች ለድምጽ መስጫው ቀን ሙሉ በሙሉ ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል። አስተባባሪው አክለውም፥ በድምጽ መስጫው እለት መራጩ ህዝብ ከዝናብና ከጸሃይ ተከልሎ ያለምንም እንግልት ድምጹን ለመስጠት የሚያስችለው ስፍራ መዘጋጀቱን አስረድተዋል። በምርጫ ጣቢያው ድንኳን ተደኩኖ ስፍራው ለመራጩ ህዝብ ምቹ መሆኑን የገለፁት ደግሞ የመናኸሪያ ቀበሌ ወጣት ማእከል ምርጫ ጣቢያ ሃላፊ አቶ ብሩክ እሸቱ ናቸው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት፣ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነገ ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል።