ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
የአብሮነትና የወንድማማችነት እሴቶችን በማጠናከር ለክልሉ ዘላቂ ሰላምና ልማት በጋራ ልንሰራ ይገባል -ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ
Dec 1, 2025 19
ጋምቤላ፤ ህዳር 22/2018 (ኢዜአ)፦ የአብሮነትና የወንድማማችነት እሴቶችን በማጠናከር ለክልሉ ዘላቂ ሰላምና ልማት በጋራ ልንሰራ ይገባል ሲሉ የጋምቤላ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ አለሚቱ ኡሞድ ገለፁ። 20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን ''ዴሞክራሲያዊ መግባባት ለህብረ ብሔራዊ አንድነት'' በሚል መሪ ሀሳብ በጋምቤላ ክልል ደረጃ በአኝዋሃ ዞን ዲማ ወረዳ በተለያዩ ዝግጅቶች በድምቀት ተከብሯል። ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ በክብረ በዓሉ ላይ እንዳሉት ህገ መንግስቱ ለብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ያጎናፀፈውን መብት በመጠቀም የክልሉን ህዝብ የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ይገኛል። በዓሉን ስናከብርም የህዝቦችን አንድነትና ወንድማማችነት የሚሸረሽሩ እንቅስቃሴዎችን በመታገልና የህዝቦችን አንድነትና አብሮነትን በማፅናት ሊሆን እንደሚገባ ተናግረዋል። በክልሉ እያጋጠሙ ያሉ ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር የተያዘውን የብልጽግና ጉዞ ዕውን ለማድረግ ያላሰለሰ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝም ገልፀዋል። በብዝሃነት ውስጥ ያለውን አንድነት በማጠናከር የክልሉን ህዝብ ሁለንተናዊ የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ጥረቶች እንደሚጠናከሩም አብራርተዋል። በየደረጃው የሚገኙ አመራሮችም ክልሉ ለጀመራቸው የዘላቂ ሰላምና የልማት ስራዎች መሳካት ግንባር ቀደም ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባም ርዕሰ መስተዳድሯ አስገንዝበዋል። የክልሉ ምክር ቤት አፈ -ጉባኤ ወይዘሮ መሠረት ማቲዎስ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት በዓሉ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ህገ-መንግስታዊ ዋስትና ያገኙበት ዕለት በመሆኑ ለክልሉ ህዝብ ልዩ ትርጉም አለው። ጋምቤላ የክልሉ ህዝቦች ተቻችለውና ተከባብረው በፍቅር አብረው የሚኖሩበት አካባቢ እንደመሆኑ መጠን ይህንን የጋራ እሴቶች ጠብቆ ለትውልዱ ማስተላለፍ ይጠበቅብናል ብለዋል። በክልል ደረጃ ህገ መንግስቱ የፀደቀበትን ዕለት በዚህ መልኩ በድምቀት ማክበራችን የህዝቦችን አንድነትና እኩልነት አጉልቶ ያሳያል ብለዋል። ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል ወይዘሮ አጁሉ ቶማስ በሰጡት አስተያየት በዓሉን የክልሉ ብሄሮች ብሔረሰቦች እና ህዝቦች በጋራ ማክበራችን አብሮነታችንና አንድነታችንን ይበልጥ ያጠናክራል ብለዋል። በዓሉ አንዱ የሌላውን ማንነት፣ ወግና እሴት እንድናውቅ እድል የሚሰጥ ከመሆኑም በላይ ለክልሉ ሰላምና ልማት መሳካት አበርክቶው የጎላ ነው ያሉት ደግሞ ሌላው የበዓሉ ታዳሚ አቶ ቱት ኒውት ናቸው። ትናንት በሲምፖዚየም የተከበረው 20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓል በጋምቤላ ክልል ደረጃ በአኝዋሃ ዞን ዲማ ወረዳ እለቱን በሚያደምቁ መርሃ ግብሮች ተከብሮ ውሏል።
20ኛው የብሔሮች፣ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በኦሮሚያ ክልል ደረጃ በቡሌ ሆራ ከተማ እየተከበረ ነው
Dec 1, 2025 73
ቡሌ ሆራ፤ ህዳር 22/2018 (ኢዜአ):- በኦሮሚያ ክልል ደረጃ 20ኛው የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በቡሌሆራ ከተማ እየተከበረ ነው፡፡ በበዓሉ ላይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አገኘሁ ተሻገር ፣የጨፌ ኦሮሚያ አፈ ጉባኤ ሰዓዳ አብዱራህማንን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ሃላፊዎች እንዲሁም የብሔሮች ፣ብሔረሰቦችና ህዝቦች ተወካዮች ታድመዋል። ቀኑ በብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ትዕይንት፣ በማርሽ ባንድና በህጻናት ትርዒቶች በቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ ስታዲየም በድምቀት እየተከበረ ነው። በዓሉ "ዴሞክራሲያዊ መግባባት ለኀብረብሄራዊ አንድነት" በሚል ርዕስ በየደረጃው በተለያዩ ዝግጅቶች በክልሉ ሲከበር ቆይቶ ዛሬ የማጠቃለያ መርሃ ግብር መሆኑም ታውቋል።
መደመራዊ የዝላይ የሽግግር ሂደት ሦስት ቁልፍ ነገሮችን ይይዛል-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Nov 30, 2025 219
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፡- መደመራዊ የዝላይ የሽግግር ሂደት ወደ ውጤት መቀየር፣ ወደ ሌላ መሻገር እና ወደ ፊት መስፈንጠር የተሰኙ ቁልፍ ጉዳዮችን እንደሚይዝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ “በመደመር መንግሥት ዕይታ የዘርፎች እመርታ” በሚል ርዕስ ለብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ስልጠና ሰጥተዋል። በዚሁ ወቅትም፤ መደመራዊ የዝላይ መንገድ ሁለት ዋና ዋና ዓላማዎች እንዳሉት ጠቅሰው፤ አንደኛው ከቀዳሚው ጋር ያለ ልዩነትን በፍጥነት ማጥበብ ሲሆን ሁለተኛው እመርታዊ እድገት ማምጣት መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም መሠረት መደመራዊ የዝላይ መንገድ ሌሎች የረገጡትን ሁሉ መርገጥ ተገቢ እንዳልሆነ፤ ውጤት ዐይተን ከዚያ መማር እንችላለን ብሎ እንደሚያነሳ ጠቁመዋል። ጊዜ ወሳጅነትንና የአርፋጅነት ፈተናን ማሸነፊያ መሆን አለበት፤ ከሌሎች ውድቀትና ስኬት መማር፣ ከሀገር ውስጥም ሆነ ከሀገር ውጭ መማር ያስፈልጋል ብሎ እንደሚያምንም አመላክተዋል። ነገር ግን እያንዳንዱን ዱካ መከተል ውጤታማ አያደርግም ብሎ ያነሳል ብለዋል። በአጠቃላይ መደመራዊ የዝላይ የሽግግር ሂደት ሦስት ቁልፍ ነገሮችን እንደሚይዝ ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር)፤ እነሱም ወደ ውጤት መቀየር፣ ወደ ሌላ መሻገር እና ወደ ፊት መስፈንጠር መሆናቸውን አብራርተዋል። ይህ ማለትም ነባር ዐቅሞችን ወደ ውጤት መቀየር፣ አዳዲስ ዘርፎች መፍጠር ወደዚያ መሻገር፣ በዘርፎች ውስጥም የሚፈጠር ሽግሽግን መከወን፣ አዳዲስ የመልማት ዐቅሞች ማውጣት፣ አዳዲስ የገበያ ዕድሎች መፍጠርን እንደሚጠይቅ አስገንዝበዋል። አክለውም፤ ያለንን ዐቅም ማዘመን፣ ወደ ዓለም መስፈንጠር፣ መዋቅራዊ ሽግግግር ማረጋገጥ፣ ዕውቀትን እንደ ምርት መጠቀም ብሎም ከፈተና ውስጥ ሊፈለቀቅ የሚችል ዕድል ካለ ችግርን ወደ ዕድል መቀየር ይጠበቃል ሲሉ አስረድተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) “በመደመር መንግሥት ዕይታ የዘርፎች እመርታ” በሚል ርዕስ ለብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ስልጠና ሰጥተዋል። በክፍል ሁለት ካነሷቸው ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል…
Nov 30, 2025 136
የሀገራዊ ብልጽግና አእማዶች የተባሉት ኢኮኖሚ (ከሁሉም ለሁሉም በሁሉም)፣ ፖለቲካ (አካታችና አሳታፊ) እና ማኅበራዊ (ትውልዳዊ ልማት) ናቸው። በችግር ትብታብ ታስረን እንዳንቀር ተስፈንጥረን ወደምንፈልገው ነገር እንድንደርስ በአንዳንድ ጉዳይ ላይ መደመራዊ ዝላይ አስፈላጊ ነው። መደመራዊ የዝላይ መንገድ ዋና ዋና ዓላማዎች ከቀዳሚው ጋር ያለ ልዩነትን በፍጥነት ማጥበብ እና እመርታዊ እድገት ማምጣት ናቸው። የትውልድ ግንባታ ስትራቴጂዎች የሚባሉት በጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ ዲጂታል ዓርበኝነት፣ የትምህርት ተሃድሶ እና የባህል ኢንዱስትሪ ናቸው። ማስተካከል፣ ማስፋፋት እና ማበርከት የመደመር ትውልድ መርሆዎች ናቸው። የመደመር መንግሥት እንቅፋት - ሐሳብ አልቦነት ነው። ሐሳብ አልቦነት ማለትም በሕዝበኝነት መታወር እና መስከር፤ በነባር ባህል መታጠርና መታሰር ፤ በጊዜያዊ ችግር መሸበርና መሰበር ማለት ነው። የሐሳብ ሉዓላዊነት- የመደመር አሸናፊነት ነው።በዚህም መሠረት አመክኗዊ ውይይትና ሙግት፣ ሚዛናዊ ትብብርና ፉክክር፣ ሐሳብን በወረቀት - ሥራን በመሬት መሆን አለበት። ፍሪሊዮን - የመደመር ቀመር ነው። ይህ ማለትም መስጠትና አገልግሎት፣ ሰውን ማትረፍና ማብቃት፣ ወደ ሰላምና ብልጽግና፣ ስለ ሀገርና ትውልድ እንዲሁም ሐሳብና ሰው በተቋም ማለት ነው።
የመደመር መንግሥት መዳረሻ ሁለንተናዊ ብልጽግና ነው -ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Nov 30, 2025 132
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፡- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የመደመር መንግሥት መዳረሻ ሁለንተናዊ ብልጽግና መሆኑን ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ “በመደመር መንግሥት ዕይታ የዘርፎች እመርታ” በሚል ርዕስ ለብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ስልጠና ሰጥተዋል። በዚሁ ወቅትም የመደመር መንግሥት መዳረሻ ሁለንተናዊ ብልጽግና መሆኑን ገልጸው፤ ሁለንተናዊ ማለትም ግብረገብነትን በማያበላሽ መልኩ ትጋትና ዘመኑን የዋጀ ብቃት ደምሮ መያዝ ነው ሲሉ አስረድተዋል። ሁለንተናዊ ብልጽግና ማለት ገንዘብ ብቻ ሳይሆን ሁሉን ነገር በውስጡ ያሟላ መሆኑንም አብራርተዋል። ይህ ማለትም የበለጸገ ግን ያልሰለጠነ፤ የሰለጠነ ግን ያልበለጸገ ሰው እንዳይኖር መትጋት ማለት መሆኑን ነው ያስረዱት። ከዚሁ ጋር በተያያዘ የሀገራዊ ብልጽግና አእማዶች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ እነሱም ኢኮኖሚ (ከሁሉም ለሁሉም በሁሉም)፣ ፖለቲካ (አካታችና አሳታፊ) እና ማኅበራዊ (ትውልዳዊ ልማት) የሚሉት መሆናቸውን አብራርተዋል። የመደመር ትውልድ ቁልፍ ጥያቄዎችም ኢትዮጵያ ምን ትምሰል?፣ መንግሥት ምን ይምሰል? እና ትውልድ ምን ይምሰል? የሚሉት መሆናቸውን ጠቁመዋል። በሌላ በኩል በመደመር ትውልድ የኢትዮጵያ መልክና ቅርጽ፤ ኅብረ ብሔራዊ አንድነት ያለባት፣ የወንድማማችነት እሴትን ያጸናች፣ የሲቪክ ባህል የጎለበተባት እና ቀጣናዊ ትስስሮችን ያጠናከረች ናት ሲሉ ገልጸዋል። ማስተካከል፣ማስፋፋት እና ማበርከት የመደመር ትውልድ መርሆዎች መሆናቸውንም አመላክተዋል። እንዲሁም በጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ ዲጂታል ዓርበኝነት፣ የትምህርት ተሃድሶ፣ የባህል ኢንዱስትሪ የትውልድ ግንባታ ስትራቴጂዎች ናቸው ብለዋል።
በከማሺ ዞን አስተማማኝ ሠላም እንዲሰፍን የሀገር ሽማግሌዎች ሚና ከፍተኛ ነው
Nov 30, 2025 128
አሶሳ፤ህዳር 21/2018(ኢዜአ)፦በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከማሺ ዞን አስተማማኝ ሠላም እንዲሰፍን የሀገር ሽማግሌዎች ሚና ከፍተኛ እንደነበር የዞኑ ነዋሪዎች ተናገሩ። የከማሺ ዞን አስተዳደር ዞን በበኩሉ ዞኑ የነበረበትን የፀጥታ ችግር በመፍታት ሙሉ በሙሉ ወደ ሠላም እንዲመለስ በመደረጉ የዞኑ ነዋሪዎች ሠላማዊ የልማት እንቅስቃሴ ላይ መሆናቸውን ገልጿል። የከማሺ ዞን በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከሚገኙ ሶስት ዞኖች አንዱ ሲሆን ባለፉት ጥቂት ዓመታት የፀጥታ ችግር ይስተዋልባቸው ከነበሩ አካባቢዎች አንዱ ነው። በአሁኑ ወቅት ግን የፀጥታ ኃይሉ ከሀገር ሽማግሌዎችና አጠቃላይ ከህዝቡ ጋር ተቀራርቦ ባከናወኗቸው በርካታ ተግባራት ዞኑ ሰላሙ ተመልሶ ህዝቡ ፊቱን ወደ ልማት አዙሯል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የዞኑ ነዋሪዎች የአካባቢው ሠላም ወደ ነበረበት እንዲመለስ የሀገር ሽማግሌዎች ከፀጥታ አካላት ጋር በመሆን ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል ብለዋል። ከዞኑ ነዋሪዎች መካከል አቶ ታደሰ ሻምበል የፀጥታ ችግሩን በሠላማዊ መንገድ ለመፍታት የፀጥታ አካላት እና የሀገር ሽማግሌዎች የማግባባት ስራ በመስራትና ውይይትን እንደ አማራጭ መፍትሔ በማድረግ የዞኑ ሠላም እንዲመለስ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። ይህም ዞኑ ወደ ልማት እንዲመለስ እና ህብረተሰቡም በግብርና፣በማዕድን ልማትና በተለያዩ የሥራ ዘርፎች በመሰማራት ተጠቃሚ እየሆነ መምጣቱን ጠቁመዋል። የከማሺ ዞን የተለያዩ ብሔር፣ ብሔረሰቦች እና ህዝቦች በመከባበርና በአብሮነት የሚኖሩበት ነው ብለዋል። የሠላምን አስፈላጊነት እና የፀጥታ ችግር የሚያደርሰውን ጉዳት ሁሉም የዞኑ ነዋሪ ተረድቷል የምትለው ደግሞ ሌላዋ የዞኑ ነዋሪ መስቀሌ ዱጉማ ነች። በአሁኑ ወቅት በዞኑ ሰፊ የልማት እንቅስቃሴ መኖሩን በመግለጽ። የከማሺ ዞን የሀገር ሽማግሌ አቶ አሻግሬ ቄሌ በበኩላቸው፤ የፀጥታ ችግሩን በውይይት ለመፍታት የተደረገው ጥረት ውጤታማ ነበር ብለዋል። በተደረገው ባህላዊ የእርቅ ስነ-ስርዓት በጫካ ሲንቀሳቀሱ የነበሩ ኃይሎች በሠላም ወደ ህብረተሰቡ እንዲቀላቀሉና በዞኑ አስተማማኝ ሠላም እንዲሰፍን መደረጉን ገልጸዋል። የከማሺ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ብጅጋ ፃፊዮ ዞኑ የነበረበትን የፀጥታ ችግር በመፍታት ሙሉ በሙሉ ወደ ሠላም እንዲመለስ በመደረጉ የዞኑ ነዋሪዎች ሠላማዊ የልማት እንቅስቃሴ ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
የበዓሉ መከበር ሀገራዊ መግባባቱ እንዲዳብርና በብዝሃነት ውስጥ ያለው አንድነት እንዲጠናከር የላቀ ሚናን ይጫወታል
Nov 30, 2025 159
ጋምቤላ፤ ህዳር 21 /2018 (ኢዜአ) ፡-የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች በዓል መከበር ሀገራዊ መግባባቱ እንዲዳብርና በብዝሃነት ውስጥ ያለው አንድነት እንዲጠናከር የላቀ ሚናን ይጫወታል ሲሉ የጋምቤላ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ወይዘሮ መሠረት ማቲዎስ ገለፁ። 20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች በዓል ''ዴሞክራሲያዊ መግባባት ለህብረ ብሔራዊ አንድነት'' በሚል መሪ ሃሳብ በክልል ደረጃ በአኝዋሃ ዞን በዲማ ወረዳ በፓናል ውይይትና ሌሎች መርሃ ግብሮች እየተከበረ ነው። ዛሬ በተካሄደው የፓናል ውይይት ላይ አፈ-ጉባኤዋ እንዳሉት የበዓሉ መከበር ሀገራዊ መግባባቱ እንዲዳብርና በብዝሃነት ውስጥ ያለው አንድነት እንዲጠናከር የላቀ ሚናን ይጫወታል። በክልሉ በርካታ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች አብሮነታቸውን በማጠናከር በጋራ እንደሚኖሩ ገልጸው የበዓሉ መከበርም ይህን መስተጋብር ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ተናግረዋል። የበዓሉ በየዓመቱ መከበር አንዱ የሌላውን ባህል፣ እሴትና ወግ እንዲረዳ የሚያደርግ በመሆኑ ዕለቱ ትልቅ ትርጉም የሚሰጠዉ ነው ብለዋል። የፓናል ውይይቱ ዋና ዓላማም ትክክለኛ በሆነው የፌደራሊዝም እሳቤ ዙሪያ ሀገራዊ መግባባትን ለማዳበር ታሳቢ ያደረገ መሆኑንም አፈ-ጉባኤዋ አስረድተዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ አለሚቱ ኡሞድ በመድረኩ ላይ እንዳሉት የክልሉ ህዝብ ህገ-መንግስቱ ያጎናፀፈውን መብት ተጠቅሞ በኢኮኖሚያዊ ፣ በማህበራዊና በፖለቲካዊ ዘርፎች ያለውን ተሳትፎና ተጠቃሚነት እያጎለበተ መጥቷል። በዓሉ በጋራ መከበሩ በጠንካራ ሀገራዊ መግባባት ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን፣ የተዛባ ትርክትን ለማስተካከልና ብዝሃነትን በአግባቡ ለማስተናገድ እንደሚያስችል ገልፀዋል። በፓናል ውይይቱ ላይ ''ዲሞክራሲና የፌዴራል ስርዓት በኢትዮጵያ፣ ተስፋዎችና ተግዳሮቶቹ'' በሚል ርዕስ ሰነድ ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። በነገዉ ዕለትም 20ኛዉ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓል በክልል ደረጃ በአኝዋሃ ዞን በዲማ ወረዳ አዘጋጅነት በተለያዩ መርሃ ግብሮች በድምቀት ይከበራል።
የመደመር መንግሥት በአራት መሠረታዊ ጉዳዮች ላይ ያጠነጥናል-ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Nov 30, 2025 154
አዲስ አበባ፤ሕዳር 21/2018 (ኢዜአ)፡- የመደመር መንግሥት መፍጠር፣ መፍጠን፣ ማብዛት እና ማጥራት በሚሉ መሠረታዊ ጉዳዮች ዙሪያ እንደሚያጠነጥን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አስገነዘቡ። “በመደመር መንግሥት ዕይታ የዘርፎች እመርታ” በሚል ርዕስ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለብልጽግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ስልጠና ሰጥተዋል። በዚሁ ወቅትም፤ የመደመር መንግሥት ሲባል አራት መሠረታዊ ጉዳዮች ማለትም መፍጠር፣ መፍጠን፣ ማብዛት እና ማጥራት የሚሉትን ነጥቦች እንደሚይዝ አስገንዝበዋል። አያይዘውም ብዙ ያልፈጠረ ጥራትን ማረጋገጥ እንደማይችል አስረድተዋል። ጥራት ያላቸው ጉዳዮች የሚወጡት ከብዙ ፈጠራ ውስጥ መሆኑንም ገልጸዋል። በሌላ በኩል ብዙ ለመፍጠር ፍጥነት እንደሚያስፈልግም ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያስረዱት። ያልፈጠነ ሰው ባለው ጊዜ በርከት ያሉ ጉዳዮች መፍጠር እንደማይችልም አመላክተዋል። ብዙ ስንፈጥር ብዙ ስንሮጥ ከእነዚያ መካከል ጥቂቶቹ ረዘም ላለ ጊዜ ለመጓዝ ጥራትን ከዚያ ውስጥ መዝዞ ለማውጣት ያግዛል ማለት ነው ሲሉም አብራርተዋል። ብዙ በመፍጠር ብሎም ብዙ ለመፍጠር በመፍጠን ነው ጥራትን የምናረጋግጠው ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) በስልጠናው ወቅት። በአጠቃላይ የመደመር መንግሥት የሚያጠነጥነው በእነዚህ እሳቤዎች ዙሪያ መሆኑንም ነው በአጽንኦት ያስገነዘቡት።
በትግራይ ክልል ዘላቂ ሰላም ለማስፈንና ልማትን ለማረጋገጥ ወጣቱ የነቃ ተሳትፎ ማበርከት አለበት -ትዴፓ
Nov 30, 2025 124
አዲስ አበባ፤ህዳር 21/2018(ኢዜአ)፦በትግራይ ክልል ዘላቂ ሰላም ለማስፈንና ልማትን ለማረጋገጥ ወጣቱ የነቃ ተሳትፎ ማበርከት እንዳለበት የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ/ ትዴፓ / ገለጸ። የቀድሞ ህወሃት በትግራይ የሚያካሂዳቸው እንቅስቃሴዎች በህዝብ ላይ እንደመቀለድ የሚወሰድ መሆኑንም ገልጸዋል። የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ/ ትዴፓ / በመጪው ምርጫ ለመወዳደር ዝግጅት እያደረገ መሆኑን አስታውቋል። የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ዋና ፀሐፊ ሙሉብርሃን ሃይሌ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የክልሉ ሕዝብ ያጋጠሙትን ተግዳሮቶች ለመፍታት ወጣቱ የነቃ ተሳትፎ ማድረግ ይጠበቅበታል። በተለይም ክልሉ ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ ወጣቱ በመጪው ምርጫ ንቁ ተሳትፎ ማድረግ እንደሚጠበቅበት ጠቁመው፤ለዚህም በፖለቲካ ሂደቱ ወጣቱ የራሱን አስተዋጽኦ ለማበርከት የሚያስችሉት ተግባራትን ፓርቲያቸው እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ ሁሉም የሚሳተፍበት በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጠ ፓርቲ ወደ ሥልጣን እንዲመጣ የማድረግ ስራ ትኩረት እንደተሰጠው አመልክተዋል። ከዚህ ውስጥም ከተለያዩ አደረጃጀቶች፣ ልሂቃን እና በክልሉ የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ጨምሮ ከሲቪክ ማሕበራት ጋር በቅንጅት የመስራት ጅማሮ መኖሩንም አስታውቀዋል። ፓርቲው ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ በመጪው ምርጫ ለመወዳደር እየሰራ መሆኑን ነው የተናገሩት። በአሁኑ ወቅት የትግራይ ሕዝብ ከምንም በላይ የሚፈልገው ሰላም፣ልማትና ዲሞክራሲ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህን ለማሳካት የጋራ ትግል እንደሚያስፈልግ ነው ዋና ፀሐፊው አቶ ሙሉብርሃን የገለጹት። ህዝቡ ያለ ስጋት ስለ ልማት እንዲያስብ የሁሉም ዜጋ ርብርብ እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል። በሌላ በኩል የቀድሞ ህወሃት በትግራይ ክልል መጪው ምርጫ እንዳይሣካ ለማድረግ የሚያከናውናቸው ተግባራት በህዝብ ላይ እንደመቀለድ የሚወሰዱ መሆናቸውን ገልጸዋል። ከህወሓት ተፈጥሯዊ ባሕርይ አኳያ ሰላማዊ ትግልን የሚሸሽና የማይፈልግ ነው ያሉት ዋና ፀሐፊው፤ የቡድኑ አባላት በሃሳብ የበላይነት የማያምኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። ይልቁንም በክልሉ ብጥብጥና ሁከት በመፍጠር ምርጫ ለማወክ፣በግርግር ስልጣን ለማግኘት እየተንቀሳቀሱ እንደሆነም አንስተዋል። ማንኛውም ወገን ለሕዝብ ሰላምና እድገት የሚያስብ ከሆነ በሕጋዊ መንገድ ተመዝግቦ ለምርጫ ራሱን ማዘጋጀት እንዳለበትም ነው የጠቀሱት።
የአየር ሀይል የተመሰረተበት 90ኛ አመት ምክንያት በማድረግ ከፍተኛ ዝግጅት የተደረገበት የአየር ላይ ትርኢት ይካሄዳል-ሌተናል ጀነራል ይልማ መርዳሳ
Nov 30, 2025 154
አዲስ አበባ፤ህዳር 21/2018(ኢዜአ)፦የአየር ሀይል የተመሰረተበት 90ኛ አመት ምክንያት በማድረግ ከፍተኛ ዝግጅት የተደረገበት የአየር ላይ ትርኢት እንደሚካሄድ የአየር ሀይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጀነራል ይልማ መርዳሳ ገለጹ። የኢትዮጵያ አየር ኃይል 90ኛ ዓመት የምስረታ በዓል በማስመልከት የ10 ኪሎ ሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ በቢሾፍቱ ከተማ ተካሂዷል። የጎዳና ላይ ሩጫው ‟ለአየር ኃይል ዕድገት በሙሉ አቅሜ እሮጣለሁ” በሚል መሪ ቃል ነው የተካሄደው። በመርሀ ግብሩ የአየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ፣ የቢሾፍቱ ከተማ ከንቲባ አለማየሁ አሰፋ፣የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ኮማንደር ስለሺ ስህን እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎች፣የሰራዊት አባላት እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ በዚሁ ወቅት፥ ሁነቱን ላዘጋጁ አካላት ምስጋና አቅርበዋል። ኢትዮጵያ ታላቅ ሀገር ናት ሲባል በምክንያት መሆኑን ጠቅሰው፤ የሰው ዘር መገኛ፣ ቅኝ ያልተገዛ ህዝብ እንዲሁም ተስማሚ የአየር ንብረት ያላት ሀገር መሆኗን ተናግረዋል። የቢሾፍቱ ከተማ 24 ሰዓት በልማት ላይ እንደምትገኝ በመጠቆም የቢሾፍቱ ከተማ እና አየር ኃይል በእጅጉ የተቆራኙ መሆናቸውን አንስተዋል። የጎዳና ሩጫው የአየር ኃይል የተመሰረተበት 90ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ መከናወኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይም ከፍተኛ ዝግጅት የተደረገበት የአየር ላይ ትርኢት እንደሚካሄድ ተናግረዋል። በተጨማሪም የተለያዩ ሀገራት አየር ኃይል አዛዦች ኮንፈረንስ እንዲሁም የአቪዬሽን ኤክስፖ የምስረታ በዓሉ አንዱ አካል መሆኑን አመላክተዋል። የከተማዋ ነዋሪዎች እነዚህን ሁነቶች በተሳካ ሁኔታ ለማጠናቀቅ ሚናቸውን መወጣት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የጎዳና ላይ ሩጫው በቀጣይ በቢሾፍቱ ከተማ በቋሚነት እንደሚካሄድ ጠቁመዋል። በውድድሩ አሸናፊ ለሆኑ አትሌቶች የአየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ የገንዘብ እና የዋንጫ ሽልማት አበርክተዋል።
የሀገር እድገት ከልካይ የሆኑ አጥሮችን መስበር ካልተቻለ ሀገራዊ እድገት ማምጣት አይቻልም - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Nov 29, 2025 184
አዲስ አበባ፤ ህዳር 20/2018(ኢዜአ)፦ የሀገር እድገት ከልካይ የሆኑ አካላዊ፣ ተቋማዊ ወይም ስርዓታዊ እንዲሁም ባህላዊ አጥሮችን መስበር ካልተቻለ ዕድገት ማምጣት አይቻልም ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በብልጽግና ፓርቲ የከፍተኛ አመራሮች ስልጠና ማጠቃለያ ላይ “በመደመር መንግሥት ዕይታ፣ የዘርፎች እመርታ” በሚል መሪ ሀሳብ በመደመር መንግሥት እሳቤዎች ዙሪያ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ በማብራሪያቸውም የሀገር እድገት ከልካይ የሆኑ አካላዊ፣ ተቋማዊ ወይም ስርዓታዊ እንዲሁም ባህላዊ አጥሮችን መስበር ካልተቻለ ዕድገት ማምጣት አይቻልም ነው ያሉት። አዲስ አበባ ከተማ እነዚህን አጥሮች መስበሩን በአብነት አንስተው በዚህም እውቀትና ገንዘብ ያለው እንዲሁም ኢንቨስት ለማድረግ የሚፈልግ ሰው መጠቀም የሚችልበት ዐውድ መፈጠሩን ተናግረዋል፡፡ ክልሎች መሰል አጥሮችን በመስበር እውቀትና ገንዘብ ያላቸውን ሰዎች መሳብ ካልቻሉ በአዲስ አበባ የተገኘውን እድገት ማሳካት እንደሚቸግራቸውም አስገንዝበዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ስለኢነርጂ ሀብትና የማምረት አቅምን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያም ኢትዮጵያ ካላት እምቅ የኢነርጂ አቅም የተጠቀመችው ውስን ብቻ መሆኑን ገልጸዋል። ኢነርጂን በብዛት ማምረት ለኢንዱስትሪ፣ ለግብርና፣ ለከተሜነት እና ለቴክኖሎጂ ግብዓት መፍጠር መሆኑንም አያይዘው ተናግረዋል። የኢትዮጵያን የኢነርጂ እምቅ ሀብት እና የማምረት አቅም ባነሱበት ማብራሪያቸውም አፍሪካ ውስጥ ከሚገኙ አስራ አምስት ትላልቅ ግድቦች መካከል አራቱ በኢትዮጵያ እንደሚገኙ ገልጸዋል። እነርሱም በ11ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ተከዜ፣ 7ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ጊቤ፣ 2ኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠውን ኮይሻ እእንዲሁም በ1ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘውን ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብን በማሳያነት አንስተዋል። በአፍሪካ ከሚገኙ 15 ትላልቅ የሀይል ማመንጫ ግድቦች መካከል በቁጥር አራቱ በኢትዮጵያ ቢገኙም ኢትዮጵያ ካላት የማምረት አቅም ጋር ሲነፃፀር ብዙ መሰራት እንደሚገባ ያሳያል ነው ያሉት። መሰልጠንን በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያም አባይ ታሪክ ነው፤ ንጋት ግን ታሪክ በመስራት የተገኘ ድል በመሆኑ ሥልጣኔ መሆኑን ገልጸዋል። እንደንጋት አይነት ስራዎችን ደጋግመን ከሰራን ሥልጣኔን መጎናጸፍ፣ ማቆየትና ማሸጋገር እንደሚቻል አስገንዝበዋል፡፡ በሥልጣኔ ጎዳና የመደመር ሚና ስብራትን መጠገን፣ መሰረት መጣል እና ሥልጣኔን ማስቀጠል የሚያስችል አቅጣጫን መቀየስ እነደሆነ ጠቁመው እነዚህን ሂደቶች ተግባራዊ ለማድረግ መነሻው ሀሳብ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። የመደመር እሳቤ ለሥልጣኔያችን ዘር ሆኖ የሚያገለግል ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ይህ እሳቤ ካለፈው ተምረንና የሚስተካከለውን አርመን፣ በዛሬው ተጠቅመንና ተመስርተን የነገውን የምንረዳበት መነጽር፣ የማይጠፋና የማይሞት ዘር መሆኑንም አስገንዝበዋል።
በክልሉ የፅንፈኛውን ቡድን የጥፋት ተልዕኮ በማምከን የሕዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ነው
Nov 29, 2025 133
ባህር ዳር፤ ህዳር 20/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የፅንፈኛውን ቡድን የጥፋት ተልዕኮ በማምከንና የሕግ የበላይነትን በማስከበር የሕዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ሀላፊ እሸቱ የሱፍ(ዶ/ር) ገለጹ። የቢሮው የ5 ዓመት ስትራቴጂክና የ2018 በጀት ዓመት ዕቅድ ላይ ያተኮረ መድረክ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የቢሮ ሀላፊው እሸቱ የሱፍ(ዶ/ር) እንዳመለከቱት፤ ጽንፈኛ ቡድኑ የታሪካዊ ጠላቶችን የጥፋት ተልዕኮ በመቀበል ህፃናትን ከትምህርት ገበታ የመነጠል፣ አርሶ አደሩ የግብርና ግብዓት በወቅቱ እንዳይደርሰው በማድረግና ሌሎች በደሎችን በማድረስ የሕዝብ ጠላትነቱን በተግባር አረጋግጧል። የቡድኑን አጥፊነት ሕዝቡ ተረድቶ ከሕግ አስከባሪዎች ጋር በመተባበር አምርሮ እየታገለው መሆኑን ተናግረዋል። ቡድኑ በመበታተን ላይ መሆኑን አንስተው፤ በሕግ ማስከበር እርምጃው የጥፋት ተልዕኮን በማምከን የሕዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራት በመከናወን ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል። መንግስት ያቀረበውን የሰላም አማራጭ በመጠቀም በርካታ የቀድሞ ታጣቂዎች በየቀኑ ወደ ሰላማዊ ኑሮ እየገቡ መሆኑንም ተናግረዋል። አሁንም የቀሩት የቀረበላቸውን የሰላም አማራጭ ዕድል መጠቀም እንደሚችሉ ጠቅሰው፤ ሆኖም በባንዳነት በመንቀሳቀስ በጥፋት ድርጊቱ ለመቀጠል የሚሞክር ካለ የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በክልሉ ሰላምን በዘላቂነት ለማፅናት ሕብረተሰቡ ፅንፈኞችን በማጋለጥ እያደረገ ያለውን ሁሉን አቀፍ ጥረት የበለጠ አጠናክሮ እንዲቀጥልም መልዕክት አስተላልፈዋል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የአስተዳደር ክላስተር አስተባባሪ አማኑኤል ፈረደ(ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የክልሉን ሰላም ለማፅናት በተወሰደው ጠንካራ የሕግ ማስከበር እርምጃ የባዳዎችና የባንዳዎችን እኩይ ዓላማ ማክሸፍ መቻሉን ተናግረዋል። በተገኘው ሰላም የሕዝቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተው፤ የክልሉ መንግስት የፀጥታ መዋቅሩን መልሶ በማደራጀት ውጤታማ ስራዎች ማከናወን ችሏል ብለዋል። መንግስት ያስቀመጣቸውን ሁለንተናዊ የልማትና የመልካም አስተዳደር ግቦች ለማሳካት የሕዝቡን ሰላምና ደህንነት በዘላቂነት ማስጠበቅ አጽንኦት የተሰጠው ጉዳይ መሆኑንም ተናግረዋል። በክልሉ የፀጥታ ስራዎችን በብቃት በመፈፀም እየተከናወኑ የሚገኙ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች በተሻለ ፍጥነትና ጥራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉ ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። በመድረኩ በየደረጃው የሚገኙ የፀጥታ ዘርፍ አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
በሀገረ መንግስት ግንባታ ሂደት ውስጥ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች አዎንታዊ ሚናቸውን ማጠናከር አለባቸው
Nov 29, 2025 118
አዳማ፤ ህዳር 20/2018(ኢዜአ)፦ በሀገረ መንግስት ግንባታ ሂደት ውስጥ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች አዎንታዊ ሚናቸውን ማጠናከር እንዳለባቸው የሰላም ሚኒስቴር አስገነዘበ። የሲቪል ማህበረሰብ በሀገር መንግስት ግንባታ ላይ የሚጠበቅባቸውን ሚና በተሻለ መወጣት በሚያስላቸው ሁኔታ ላይ የመከረ መድረክ በአዳማ ከተማ ተካሄዷል። የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ኬይረዲን ተዘራ (ዶ/ር) እንደገለፁት በሀገረ መንግስት ግንባታ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ ነው። በተለይ በሰላምና ሀገረ መንግሥት ግንባታ ዙሪያ መንግስታዊና መንግስታዊ ካልሆኑ የሲቪል ተቋማትና ድርጅቶች ጋር በቅርበት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ ድርጅቶቹ በሰላም፣ በመቻቻልና አብሮነት እንዲሁም በጋራ እሴቶች ማጎልበት ላይ እየሰሩ መሆናቸውንና ይህንንም ማጠናከር እንዳለባቸው ገልጸዋል። በተለይም የሀገርን ብሔራዊ ጥቅምን ማስጠበቅ፣ በጋራ እሴትና ሀገራዊ ማንነትን ማስረፅ ላይ በትኩረት እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰው፣ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ጋርም የጋራ እሴትና አብሮነትን ማጎልበት በሚቻልበት ሁኔታዎች ላይ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አመልከተዋል። በቀጣይም የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በሀገረ መንግስትና በሰላም ግንባታ ላይ የሚወጡትን አዎንታዊ ሚና እንዲያጠናክሩ አስገንዝበዋል። የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ሳምሶን ቢራቱ በበኩላቸው ሰላም ለሀገር ዘላቂ ልማትና ዕድገት ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ሰላምን በማፅናት እና በአገረ መንግስት ግንባታ ሂደት ድርሻቸውን እየተወጡ ነው ብለዋል። ለዚህም በህጋዊ መንገድ ተመዝግበው እየተንቀሳቀሱ ካሉ 5ሺህ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጀቶች መካከል 300 የሚሆኑት በሰላም ጉዳይ ላይ እየሰሩ መሆኑን በማሳያነት ጠቅሰዋል።
ቀኑ የወል ትርክት ግንባታን ይበልጥ ለማጠናከር ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Nov 29, 2025 123
ድሬዳዋ ፤ ሕዳር 20/2018 (ኢዜአ)፡- የብሔሮች ፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በዓል መከበር የወል ትርክትን በመገንባት ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን ይበልጥ ለማጠናከር ምቹ ሁኔታ መፍጠሩ ተገለጸ። የ20ኛው የብሔሮች ፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በዓል ዛሬ በድሬዳዋ አስተዳደር ተከብሯል ። በበዓሉ ላይ የድሬዳዋ አስተዳደር ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ወይዘሮ ፈትህያ አደን፤ በዓሉ ብሔሮች፣ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ሕብረ ብሔራዊ አንድነታቸውን ያፀኑበት እንደሆነ አንስተዋል። ዜጎች ጠንካራ ሀገረ መንግስት በመገንባት የበለፀገች ኢትዮጵያን ዕውን ለማድረግ እንዲተጉ ምቹ መደላደል የተፈጠረበት መሆኑን ገልጸዋል። በተለይ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በጠንካራ ሕብረ ብሔራዊ አንድነት በገጠርና በከተማ ዘርፈ ብዙ ውጤቶች መመዝገባቸውን ተናግረዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር በበኩላቸው ፤ የብሔሮች ፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ቀን በዓል መከበሩ ሕብረ ብሔራዊ አንድነት ይበልጥ ለማጠናከር ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል። እንቅፋት የነበረውን ነጠላ ትርክት በማስቀረት የወል ትርክትን በመገንባት ተጨባጭ ውጤት ማምጣት መቻሉን ተናግረዋል ። ዘንድሮ በድሬዳዋ ገጠርና ከተማ የተከበረው በዓሉ የተጀመሩ ተስፋ ሰጪ ውጤቶችን በላቀ ደረጃ ለማሳደግ ይበልጥ መነሳሳት የተፈጠረበት መሆኑን ጠቅሰው፤ ሕብረተሰቡ ሕብረ ብሔራዊ አንድነቱን አፅንቶ ለተሻለ ለውጥ እያደረገ ያለውን ተሳትፎ እንዲያጠናክር መልዕክት አስተላልፈዋል ።
በዞኖቹ የሰፈነው ሰላም ሕብረተሰቡ ወደ ልማት እንዲመለስ አስችሏል
Nov 29, 2025 169
ነቀምቴ፤ ሕዳር 20/2018 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል ሶስት የወለጋ ዞኖች የሰፈነው ሰላም ሕብረተሰቡ ፊቱን ወደ ልማት በመመለስ ውጤታማ ተግባራት እንዲያከናውን ያስቻለው መሆኑን የዞኖቹ አመራሮች አስታወቁ። ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የምዕራብ ወለጋ፣ የምስራቅ እና ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞኖች አመራሮች በአካባቢው የሰፈነው ሰላም ለልማት ስራዎች ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል ብለዋል። የምዕራብ ወለጋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ገመዳ ተፈራ፣ በዞኑ ሕብረተሰቡ ከፀጥታ አካላት ጋር ተቀናጅቶ በመስራቱ ሰላም መስፈኑን ገልጸዋል። ቀደም ባሉት ዓመታት በዞኑ በነበረው የጸጥታ ችግር የልማት ስራዎችን ማከናወን አዳጋች እንደነበር ጠቅሰው ፤ በሰፈነው ሰላም ሕዝቡ ትኩረቱን የልማት ስራ ላይ አድርጓል ነው ያሉት። የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ መደበኛ የግብርና ልማት ስራዎችን በትኩረት ከማከናወን ባሻገር የተቋረጡ የመሰረተ ልማት ዝርጋታ ስራዎች ዳግም እንዲጀመሩ ማስቻሉን ተናግረዋል። በተጨማሪም ዞኑ ለኢንቨስትመንት ያለውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ባለሀብቶች የማዕድን ልማትን ጨምሮ በተለያዩ የልማት ስራዎች ላይ እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ የተጀመሩ ተስፋ ሰጪ የገጠር እና የከተማ ልማት ስራዎች የበለጠ እንዲጠናከሩ የተገኘውን ሰላም ዘላቂ ለማድረግ ርብርቡ ይቀጥላል ብለዋል። የምስራቅ ወለጋ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ደሱ ለሚ በበኩላቸው፤ በዞኑ የነበረው ችግር ተወግዶ ሰላም ሰፍኗል ብለዋል። የሰፈነው ሰላም ለልማት ስራዎች መፋጠን ምቹ ሁኔታ በመፍጠሩ ወጣቶችም የስራ እድል ተጠቃሚ ሆነው ራሳቸውን ለመለወጥ እየተጉ መሆኑን አንስተዋል። በዞኑ ሕዝቡን በማሳተፍ ሰፋፊ የግብርና ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰው ፤ የማዕድን ፣ የቱሪዝም መዳረሻ ልማት እና ሌሎች ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ ብለዋል። የዞኑ ሕዝብ ከፀጥታ አካላት ጋር በመተባበር የጀመረውን ዘላቂ ሰላም የማስፈን ስራ አጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። የሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን አሙሩ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ደረጄ ወርቁ፣ በወረዳው ሰላም በመስፈኑ ሕብረተሰቡ የልማት ስራውን በሙሉ አቅሙ እያከናወነ ይገኛል ብለዋል። በወረዳው እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎችም ተስፋ ሰጪ መሆናቸውን አመልክተው፤ የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራም እየተከናወነ መሆኑን አንስተዋል። የሰላም መንገድን የመረጡ የቀድሞ ታጣቂዎችም የተሃድሶ ስልጠና ወስደው በተለያዩ የልማት ስራዎች እየተሳተፉ መሆኑን ገልጸዋል።
የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ የተለያዩ ውሳኔዎችን አሳለፈ
Nov 29, 2025 157
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 20/2018(ኢዜአ)፦ የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 50ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ምክር ቤቱ በ50ኛ መደበኛ ስብስባው ያሳለፋቸው ውሳኔዎች የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 50ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ፡፡ 1. ምክር ቤቱ በቅድሚያ የተወያየው በዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ ላይ ነው፡፡ ስትራቴጂው ለዜጎች አዳዲስ ዕድሎችን ለመፍጠር፣ የቴክኖሎጂ አቅምን ለማሳደግና መሰረተ ልማቶቹን ለማስፋፋት፣ መልካም አስተዳደር ለማስፈንና የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማፋጠን እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችን በተሻለ መንገድ ማሳካትን ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡ ምክር ቤቱም በስትራቴጂው ላይ በሰፊው ከተወያየበት በኋላ በምክር ቤቱ ከጸደቀበት ቀን ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረግ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 2. ከዚያም ምክር ቤቱ የተወያየው ከዓለም አቀፍ የልማት ማህበር ጋር በተፈረሙ ሁለት የፋይናንስ ድጋፍ ስምምነቶች ላይ ነው፡፡ የመጀመሪያው ዘላቂ እና ንፁህ የኢነርጂ ተደራሽነት ለውጥን ለማፋጠን ፕሮግራም ማስፈፀሚያ የሚውል 294,900,000 ኤስ. ዲ. አር የብድር ስምምነት ሲሆን የ6 አመት የችሮታ ጊዜን ጨምሮ በ38 አመታት ተከፍሎ የሚጠናቀቅ ነው፡፡ ሁለተኛው የምስራቅ አፍሪካ የክህሎት ትራንስፎርሜሽን እና ቀጠናዊ ውህደት ፕሮጀክት ማስፈፀሚያ የሚውል ተጨማሪ 20,000,000 ኤስ. ዲ. አር የብድር ስምምነት ሲሆን የ6 አመት የችሮታ ጊዜን ጨምሮ በ31 አመታት ተከፍሎ የሚጠናቀቅ ነው፡፡ ሁለቱም ብድሮች ከወለድ ነጻ እና 0.75% የአገልግሎት ክፍያ የሚከፈልባቸው ናቸው፡፡ ምክር ቤቱም የብድር ስምምነቶቹ ከአገራችን የብድር አስተዳደር ስትራቴጂ ጋር የሚጣጣሙ መሆናቸውን በማረጋገጥ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፉ ወስኗል። 3. በመቀጠል ምክር ቤቱ የተወያየው የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን እና የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቴአትር ለሚሰጧቸው ልዩ ልዩ አገልግሎቶች የሚከፈሉ የአገልግሎት ክፍዎችን ለመወሰን በቀረቡ ሁለት ረቂቅ ደንቦች ላይ ነው፡፡ ተቋማቱ አገልግሎት ለመስጠት የሚያወጡትን ወጪ ሸፍነው ገቢያቸውን በማሳደግ ጥራት ያለው አገልግሎት በመስጠት የተገልጋይ እርካታን ማሳደግ በማስፈለጉ የተገልጋዩን አቅም ባገናዘበ መልኩ የአገልግሎት ክፍያ ተመን ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በረቂቅ ደንቦቹ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ታትመው ከወጡበት ቀን ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረጉ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 4. ቀጥሎም ምክር ቤቱ የተወያየው በአራት የሁለትዮሽ ስምምነቶች ላይ ነው፡፡ የመጀመሪያው ከህዝባዊት ቻይና ሪፐብሊክ መንግስት ጋር በወንጀል ጉዳዮች የጋራ የህግ ትብብር ለማድረግ የተደረገ ስምምነት ነው፡፡ ሌሎቹ ሁለት ስምምነቶች ከህዝባዊት ቻይና ሪፐብሊክ መንግስት እና ከብራዚል ፌዴራላዊ ሪፐብሊክ መንግስት ጋር ፍርደኞችን ለማስተላለፍ የተደረጉ ናቸው፡፡ ሌላው ከደቡብ አፍሪካ ሪፐብሊክ መንግስት ጋር የተደረገው የአሳልፎ መስጠት ስምምነት ነው፡፡ ምክር ቤቱም ስምምነቶች ቢጸድቁ ኢትዮጵያ ከሀገራቱ ጋር ዉጤታማ የወንጀል መከላከል የሁለትዮሽ ትብብር የሕግ ማዕቀፍ ለመፍጠር የሚያስችላት መሆኑን በመገንዘብ ረቂቅ አዋጆቹ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፉ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 5. ሌላው ምክር ቤቱ የተወያየበት አጀንዳ የኤሌክትሮኒክ ፊርማ ረቂቅ ደንብ ነው፡፡ የኤሌክትሮኒክ ፊርማ አዋጅ ቁጥር 1072/2010ን ሙሉ ለሙሉ ስራ ላይ ለማዋል የሚያስፈልጉ ስርዓቶችን በአዋጁ እና በተሻሻለው የኤሌክትሮኒክ ፊርማ አዋጅ ቁጥር 1358/2017 መሰረት ግልፅ እና ተጠያቂነት በሰፈነበት መልኩ ለመተግበር እንዲያስችል ሆኖ ደንቡ ተዘጋጅቶ ቀርቧል። ምክር ቤቱም በደንቡ ላይ በሰፊው ከተወያየበት በኋላ በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረግ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 6. በመጨረሻም ምክር ቤቱ የተወያየው የኢሚግሬሽን የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንብ ቁጥር 114/1997 ለማሻሻል በቀረበ ደንብ ላይ ነው፡፡ ተቋሙ በአዋጅ የተሰጠውን ተግባርና ሀላፊነት ለመወጣት እንዲያስችለው ደንቡ ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በደንቡ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረግ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡
በከማሺ ዞን የነበረው የፀጥታ ችግር ተፈቶ ሰላም መስፈኑ ህብረተሰቡን የልማት ተጠቃሚ አድርጓል
Nov 29, 2025 124
አሶሳ ፤ ሕዳር 20/2018 (ኢዜአ)፡-በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከማሺ ዞን የነበረው የፀጥታ ችግር ተፈቶ ሰላም መስፈኑ ህብረተሰቡን የልማት ተሳታፊና ተጠቃሚ ማድረጉን ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ። 20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ህዝቦች ቀን የማጠቃለያ በዓል "ዲሞክራሲያዊ መግባባት ለሕብረ ብሔራዊ አንድነት" በሚል መሪ ቃል በክልሉ ከማሽ ዞን ከማሺ ከተማ ተከብሯል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን እንደተናገሩት፤ በከማሺ ዞን በነበረ የሠላም እጦት የልማት ስራዎች በሚፈለገው ልክ እየተከናወኑ አልነበረም። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ህብረተሰቡ ለሠላም ባሳየው ቁርጠኝነት በዞኑ ሠላም ማረጋገጥ መቻሉንና ይህንንም ማስቀጠል እንደሚገባ ተናግረዋል። የፀጥታ አካላት፣ የሀገር ሽማግሌዎች እና የሀይማኖት አባቶች ችግሮች በውይይት እንዲፈቱና በዞኑ ሠላም እንዲሰፍን የነበራቸው ሚና ከፍተኛ እንደነበርም አቶ አሻድሊ አስታውሰዋል። በአሁኑ ወቅት በዞኑ የሰፈነውን ሠላም በመጠቀም ህብረተሰቡ በእርሻ፣ በማዕድን እና በተለያዩ የልማት ሥራዎች እየተሳተፈ ተጠቃሚ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል። የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓል በክልል ደረጃ በዞኑ መከበሩም የህዝቦችን አብሮነት ለማጉላትና ወንድማማችነትን ለማጠናከር እንደሚያግዝ አቶ አሻድሊ ጠቁመዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት አፈጉባኤ አስካለች አልቦሮ በበኩላቸው፤ በዞኑ የተለያዩ ብሔሮችና ብሔረሰቦች በአብሮነት በጋራ እንደሚኖሩ ገለፀው፣ በዓሉ ይህንን ለማጠናከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል። በዓሉ ብሔር፣ ብሔረሰቦች ማንነታቸውን የሚያንፀባርቁበት እንዲሁም በጋራ ጉዳይ ላይ አንድነታቸውን የሚያጸኑበት ሊሆን ይገባል ነው ያሉት። 20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች እና ህዝቦች ቀን ኢትዮጵያውያን በሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ በጋራ መቆም ባለባቸው ወቅት የሚከበር መሆኑም ልዩ ያደርገዋል ብለዋል። በከማሺ ዞን የተገኘው ሠላም ህብረተሰቡ የአካባቢውን ፀጋ አልምቶ ተጠቃሚ እንዲሆን እያስቻለ ነው ያሉት ደግም የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ብጅጋ ፃፊዮ ናቸው። እንደ አስተዳዳሪው ገለጻ ዞኑ የተለያዩ ብሔሮችና ብሔረሰቦች በአብሮነት የሚኖሩበት እና በአሁኑ ወቅትም አስተማማኝ ሠላም የሰፈነበት ነው። በዓሉ በፓናል ውይይት እና በተለያዩ ስፖርታዊ ዝግጅቶች እየተከበረ የቆየ ሲሆን በማጠቃለያውም የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ በክልሉ የሚገኙ የብሔር ብሔረሰቦች ተወካዮች እንዲሁም የከማሺ ከተማ ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ የዓለም አቀፍ የንግድ መስመሮች አካል መሆን አለባት-የፈረንሣይ የምድር ኃይል አዛዥ ጄነራል ፒየር ሺል
Nov 28, 2025 222
አዲስ አበባ፤ ህዳር 19/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የዓለም አቀፍ የንግድ መስመሮች አካል መሆን እንዳለባት የፈረንሣይ የምድር ኃይል አዛዥ ጄነራል ፒየር ሺል ገለፁ። ከቀናት በፊት በሁለትዮሽ ወታደራዊ ጉዳዮች ከኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ጄነራል መኮንኖች ጋር የመከሩት ጄነራል ፒየር ሺል የተለያዩ ተቋማትን ከጎበኙ በኋላ ከጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ጋርም ተወያይተዋል። "ኢትዮጵያ የባህር በር በሰላማዊ መንገድ ለማግኘት ያላትን ፍላጎት እንዴት ይመለከታሉ?" በሚል ከመከላከያ ሚዲያ ጋዜጠኞች ለተነሳላቸው ጥያቄ ምላሽ የሰጡት የፈረንሣይ የምድር ኃይል አዛዥ ጄነራል ፒየር ሺል፤ "ኢትዮጵያ በጣም ትልቅ ሐገር ናት፣ በጣም ትልቅ የኢኮኖሚ ኃይልና ሕዝብም ያላት በመሆኑ የዓለም አቀፍ የንግድ መስመሮች አካል መሆን አለባት ብለዋል። ከኢትዮጵያ ጋር የተካሄደው ወታደራዊ ትብብር ዋነኛ ዓላማም ፈረንሳይ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ትብብር ለማሻሻል አዲስ አበባ በመገኘቴ በጣም ኮርቻለሁ ብለዋል። ስለዚህ ትብብራችን በዋናነት የወታደራዊ ቁሳቁስ ድጋፍ ፣የሠላም ማስከበር ሥራዎች፣ የፈንጅ አወጋገድ ተግባራት ላይ፣ በሠው ኃይል ሥልጠና እና በሌሎችም ነው" ብለዋል። ጄነራል ፒየር ሺል ኢትዮጵያ የቀጠናውን ደኅንነት ለማስጠበቅ ዋነኛ ተዋናይ መሆኗን ገልፀው፣ የኢትዮጵያ ተሳትፎ እጅግ አስፈላጊ መሆኑንና እንደ ፈረንሣይ ሠራዊት ተወካይ የኢትዮጵያን ሠራዊት እንደሚደግፉም አንስተዋል። የኢትዮጵያን ሠራዊት ተሣትፎ በማድነቅ "ኢትዮጵያ በጣም ትልቅ ሐገር ናት፣ በጣም ጠንካራና ትልቅ ሠራዊትም አላት ከዚህ ሠራዊት ብዙ የምንማረው ነገር አለ ሲሉም አስረግጠው መናገራቸውን የመከላከያ ኦንላይን ሚዲያ ለኢዜአ የላከው መረጃ ያመለክታል። ከሰሞኑ በአዲስ አበባ የሚገኘው የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ዋናው መምሪያ የዓለም ኃያላንን ጨምሮ የተለያዩ ሐገራት የጦር መሪዎችን አስተናግዷል።
ትልልቅ የልማት አጀንዳዎችን ለማሳካት የኅብረተሰቡን ተሳትፎ የሚያጎለብቱ የተግባቦት ሥራዎችን ማጠናከር ይገባል-ከፍተኛ አመራሮች
Nov 28, 2025 168
አዲስ አበባ፤ህዳር 19/2018(ኢዜአ)፦ትልልቅ የልማት አጀንዳዎችን ለማሳካት የኅብረተሰቡን ተሳትፎ የሚያጎለብቱ የተግባቦት ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ገለጹ። በብልፅግና ፓርቲ የፌዴራል ተቋማት አደረጃጀቶች የኢኮኖሚ ክላስተር አዘጋጅነት የፖለቲካ ትንተና፣ማህበራዊ ሚዲያና ሁኔታ ትንተና ላይ በብልፅግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የአሰልጣኞች ስልጠና መርሃ ግብር ተካሂዷል። በሥልጠና መርሃ ግብሩ ላይ በፌደራል ተቋማት አደረጃጀቶች የኢኮኖሚ ክላስተር የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊዎችና የጽህፈት ቤት ኃላፊዎች ተሳትፈዋል። የኢንዱስትሪ ሚኒስትርና በብልፅግና ፓርቲ የፌዴራል ተቋማት አደረጃጀቶች የኢኮኖሚ ክላስተር ሰብሳቢ አቶ መላኩ አለበል እንዳሉት፤ አመራሩ በሪፎርም ሥራዎች በመታገዝ ትልልቅ የልማት ግቦችን ለማሳካት እየተጋ ነው። እነዚህ የልማት ግቦች የሚሳኩት በሕዝቡና በመንግሥት መካከል መሰናሰል ሲፈጠር ነው ያሉት አቶ መላኩ፥ ህብረተሰቡን በልማት አጀንዳዎች ላይ በተሻለ መልኩ የሚያሳተፉ የተግባቦት ሥራዎችን በትኩረት ማከናወን ይገባል ብለዋል። አመራሩ እየተለዋወጠ ባለው የዓለም ሁኔታ ያሉ ዕድሎችን ለመጠቀም ወቅቱን የዋጀ እውቀት በመጨበጥ ህዝቡን በውጤታማነት የማሳተፍ ሥራን ማጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል። ሥልጠናው በመረጃ ላይ በመመስረት ከሕዝቡ ጋር ይበልጥ ተናቦ ለመስራት ምቹ አውድ የሚፈጥር መሆኑን አብራርተዋል። የብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ምክትል ኃላፊ አቶ ሙሳ አህመድ በበኩላቸው፥ በመደመር መንግሥት እይታ ፈጣንና ፈጠራ የታከለበት አገራዊ አድገት ለማረጋገጥ ግብ ተይዞ ወደ ሥራ ተገብቷል። ግቡን በውጤታማነት ለማጠናቀቅ በየጊዜው የፖለቲካ ትንተና ላይ የተመሰረቱ እርምጃዎች መውሰድ እንደሚገባ ጠቁመው፥ ለዚህም አመራሩ ራሱን ዝግጁ ማድረግ እንዳለበት አመልክተዋል። የብልፅግና ፓርቲ ፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ምክትል ኃላፊ መሀመድ እድሪስ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ የኢኮኖሚ አመራሩ አካታች ኢኮኖሚ ግንባታ፣ ፍትሐዊ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትና መሰል ጉዳዮች ላይ አጀንዳ ቀርጾ መሥራት ይጠበቅበታል። የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ፣ የከተሞች ፎረምን ጨምሮ ሕዝቡን በማሳተፍ በውጤታማነት እየተተገበሩ ያሉ አጀንዳዎች መኖራቸውን ጠቅሰው፥ መሰል ሥራዎችን ማጠናከር እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። አመራሩ ፖሊሲዎችን ወደ አጀንዳነት መቀየር ላይ በሰፊው ሊሰራበት የሚገባው ጉዳይ ነው ብለዋል። በብልፅግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የብልፅግና ስትራቴጂ ጉዳይ ዋና ዳይሬክተር ተተካ በቀለ በበኩላቸው፤ የድህረ እውነት ፈተናዎች የሆኑትን ሀሰተኛ መረጃና የጥላቻ ንግግርን መታገል ላይ አመራሩ በቅንጅት ሊሰራ እንደሚገባ ጠቁመዋል።
ተማሪዎች ህብረ ብሔራዊ አብሮነትን እንዲላበሱ የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Nov 28, 2025 126
አዲስ አበባ፤ ህዳር 19/2018(ኢዜአ)፦ተማሪዎች ኢትዮጵያዊ ህብረ ብሔራዊነት አብሮነትን እንዲላበሱ የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው ርዕሳነ መምህራን ገለጹ። በየዓመቱ ህዳር 29 የሚከበረው የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን ዜጎች የአካባቢያቸውን አለባበስ፣ አመጋገብ፣ ቋንቋ፣ ባህልና እሴት የሚያስተዋውቁበት ታላቅ ኩነት ነው። ኢዜአ የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በትውልዱ እንዲሰርጽ እና ህብረ ብሔራዊ አብሮነት እንዲጎለብት የትምህርት ተቋማት ሚናን በተመለከተ የትምህርት ባለሙያዎችን አነጋግሯል። የቂሊንጦ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር ኢሳያስ ገብረሚካኤል፤ ኢትዮጵያ ብዝሃ ባህል ያላት በመሆኑ ይህንኑ ሀብት ለዓለም ለማስተዋወቅ ቀኑ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ጠቅሰዋል። የትምህርት ዘርፉ ተዋናዮች ትውልዱ የኢትዮጵያን ህብረ ብሔራዊ ውበት በአግባቡ በመገንዘብ ሀገሩን በተገቢው ልክ እንዲያውቅ የማስቻል አደራ አለብን ብለዋል። የአጋዚያን ቁጥር ሶስት ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህርት ገነት ፊጣ በበኩላቸው፤ ቀኑ ትውፊቱን ጠብቆ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ በጋራ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ ለዚህም ሁላችንም የሌላውን ባህል የማክበር ልማዳችንን ማጠናከር አለብን ሲሉ ተናግረዋል። በተለይም ተማሪዎች የብሔር ብሔረሰቦችን ብዝሃ ባህል እና ማንነት በአግባቡ እንዲያውቁ ቀኑን መሰረት በማድረግ ግንዛቤአቸውን የማሳደግ ስራ እየሰራን እንገኛለን ብለዋል። የኮከበ ፅባህ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር ደለለኝ አስማረ እንደሚሉት፤ ቀኑ ቀጣይነት ባለው መልኩ መከበሩ በህዝቦች መካከል ያለውን መልካም መስተጋብር የሚያጠናክር ነው። በዚሀም ተማሪዎች የብሔሮች ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን መከበር ያለውን ሀገራዊ ፋይዳ እንዲገነዘቡ የሚያስችሉ ስራዎችን እያከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። ተማሪዎች የብሔሮችና ብሔረሰቦችን ባህል፣ ወግና እና እሴት በጭውውትና በክበባት አማካኝነት እንዲገነዘቡ እየሰሩ መሆኑን የድልበር አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ምክትል ርዕሰ መምህር ተመስገን ቶሊና አስታውቀዋል። 20ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በዓል "ዲሞክራሲያዊ መግባባት ለህብረ ብሔራዊ አንድነት" በሚል መሪ ሃሳብ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አስተናጋጅነት ህዳር 29 ቀን 2018 ዓ.ም በሆሳዕና ከተማ ይከበራል።