ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
የአውሮፓ ሕብረት ከኢትዮጵያ ጋር በሁሉም ዘርፍ ያለውን ስትራቴጂክ ትብብር ለማስፋት ቁርጠኛ ነው
Jul 15, 2026 382
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦የአውሮፓ ሕብረት ከኢትዮጵያ ጋር በሁሉም ዘርፍ ያለውን ስትራቴጂክ ትብብር ለማስፋት ቁርጠኛ መሆኑን የአውሮፓ ሕብረት የውጭ ጉዳይና የደኅንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይና የአውሮፓ ኮሚሽን ምክትል ፕሬዝዳንት ካያ ካላስ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከአውሮፓ ሕብረት የውጭ ጉዳይና የደኅንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይና የአውሮፓ ኮሚሽን ምክትል ፕሬዝዳንት ካያ ካላስ ጋር ፍሬያማ ውይይት አድርገዋል። በውይይታቸውም በአውሮፓ ሕብረትና በአፍሪካ መካከል ያለውን ግንኙነት ማጠናከር ላይ በመምከር፣ በጋራ ጥቅሞችና ቅድሚያ በሚሰጣቸው ቁልፍ ጉዳዮች ላይ ሃሳብ ተለዋውጠዋል። በተጨማሪም በቀጣናዊ እና ትኩረት በሚሹ ጉዳዮች ላይ ተመስርተው ኢኮኖሚያዊ ትብብርን ይበልጥ ለማሳደግና ለማስፋፋት በሚያስችሉ መንገዶች ላይ መክረዋል። በተመሳሳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ጌዲዎን ጢሞቲዎስ ከአውሮፓ ሕብረት የውጭ ጉዳይና የደኅንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይና የአውሮፓ ኮሚሽን ምክትል ፕሬዝዳንት ካያ ካላስ ጋር ተወያይተዋል። በውይይታቸውም በኢትዮጵያና በአውሮፓ ሕብረት መካከል ያለውን የዘመናት ዲፕሎማሲያዊ ወዳጅነት የበለጠ ለማጠናከር፣ እንዲሁም በጋራ ጥቅም እና በአጋርነት ለመስራት ያላቸውን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል። የኮሚሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት ካያ ካላስ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የአዲስ አበባ ጉብኝታቸው ሕብረቱ የኢትዮጵያንና የአፍሪካን ስትራቴጂክ አጋርነት የበለጠ ለማጠናከር የሚያስችሉ ግብዓቶች የተገኙበት ነው። ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዎን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ጋር የነበራቸው ውይይት የኢትዮጵያንና የሕብረቱን አጋርነት ወደ ላቀ ምዕራፍ ለማሸጋገር እንደሚያስችል ገልጸዋል። አያይዘውም፣ የአውሮፓ ሕብረት በኢትዮጵያ የሚኖረውን የኢንቨስትመንት፣ የዲጂታል አስተዳደር፣ የታዳሽ ኃይል እና የሌሎች ዘርፎች ትብብር የበለጠ ለማስፋፋት ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጠዋል። የአውሮፓ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ ያላቸው ፍላጎት እያደገ መምጣቱም የንግድ ተቋማቱ በኢትዮጵያ ኢንቨስት ለማድረግና ሥራዎቻቸውን ለማስፋፋት ትልቅ ዕድል እየፈጠረ መሆኑን ተናግረዋል። ይህንን ዕድልም ለሁለቱም ወገኖች ተጠቃሚነት ለማዋል እንደሚሰራ ተገልጿል። የዲጂታል ቴክኖሎጂዎች አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻልና አዳዲስ የኢኮኖሚ ዕድሎችን ለመፍጠር እንደሚያግዙ ገልጸዋል። ኢትዮጵያና የአውሮፓ ሕብረት በዲጂታል አስተዳደር ዘርፍ ያላቸውን ትብብር እንደሚያጠናክሩ አመላክተዋል። በኢትዮጵያ ያለውን እምቅ የታዳሽ ኃይል ሀብት በመጥቀስ፤ ኢትዮጵያና የአውሮፓ ሕብረት በዘርፉ የቴክኖሎጂ ሽግግር ላይ በጋራ በመስራት ለጋራ ተጠቃሚነት ትልቅ ዕድል መፍጠር እንደሚችሉ አስረድተዋል። ሕብረቱ በአገሪቱ የጥሬ ዕቃዎች ላይ እሴት መጨመርን በመደገፍ የኢንዱስትሪ ልማት እንዲስፋፋ እንደሚያግዝ አረጋግጠዋል። ይህም ለሥራ ዕድል ፈጠራ መስፋፋት የሚኖረውን ወሳኝ ሚና ጠቁመዋል።
በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታን የሚያጎለብቱ ተምሳሌታዊ እርምጃዎች እየተወሰዱ ነው
Jul 15, 2026 291
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታን የሚያጎለብቱ ተምሳሌታዊ እርምጃዎች እየተወሰዱ እንደሚገኝ የፓርላማ መረጃ ደኅንነት ፎረም ተሳታፊ እና የምሥራቅና ደቡባዊ አፍሪካ አካውንታቢሊቲ ላብ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ማክዶናልድ ሌዋኒካ ገለጹ። ኢትዮጵያ ለዘመናት የቆዩ አለመግባባቶችንና ልዩነቶችን ለመፍታት፣ እንዲሁም ብሔራዊ መግባባትን በመፍጠር ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ሀገራዊ ምክክር እያካሄደች ትገኛለች። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽንም ባለፉት አራት ዓመታት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች እና በውጭ ሀገር ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዘንድ የአጀንዳ ማሰባሰብ ሥራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል። በዚህም መሠረት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ዛሬ ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ በይፋ ተጀምሯል። የምሥራቅና ደቡባዊ አፍሪካ አካውንታቢሊቲ ላብ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ማክዶናልድ ሌዋኒካ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ብሔራዊ መግባባትን የሚገነባ የዴሞክራሲ መንገድ ነው። አክለውም፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ በመሠረታዊ ሀገራዊ ችግሮች ላይ ለመመካከርና መፍትሔ ለመስጠት በጉባኤው መሰባሰቡ ተምሳሌታዊ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ስኬት እና የሀገራዊ ምክክር ጉባኤው ወደ መካሄድ መሸጋገሩ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታን የሚያጎለብቱ ወሳኝ እርምጃዎች መሆናቸውን ገልጸዋል። በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ስኬት፣ የበርካታ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች አባላት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ውክልና ማግኘታቸው የዴሞክራሲ ባህልን ለማጎልበት ከፍተኛ ፋይዳ እንደሚኖረውም ጠቁመዋል።
በሲዳማ ክልል የህዝብና የአመራር አቅምን በማቀናጀት የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎችን ማሳካት ተችሏል
Jul 15, 2026 283
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ):-በሲዳማ ክልል የህዝብና የአመራር አቅምን በማቀናጀት የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎችን ማሳካት መቻሉን የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ ገለጹ፡፡ ''ከምርጫ ድል ማግስት ጠንካራ መንግስት'' በሚል መሪ ቃል የክልሉ የ2018 በጀት ዓመት የመንግስትና የፓርቲ ሥራዎች አፈጻጻምን የሚገመግም መድረክ በሀዋሳ ከተማ ተካሂዷል፡፡ የክልሉ የመንግስት ዋና ተጠሪ አቶ አብርሃም ማርሻሎ በወቅቱ እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ የአመራርና የህዝብ አቅምን በማቀናጀት የግብርና ምርትና ምርታማነትን የማሳደግና ኢንዱስትሪውን በተገቢው በመምራት የዋጋ ግሽበትን መቆጣጠር ተችሏል። በተለይ የኑሮ ውድነትን ለማርገብ የግብርና ምርታማነትን ማሳደግን ጨምሮ ገበያ ተኮር ምርቶችን የማምረት ግብ ተይዞ ወደ ሥራ መገባቱን ጠቅሰው፣ በየደረጃው ያለው አመራር ተገቢውን ድጋፍ በማድረጉ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል፡፡ ውሃ አጠር በሆኑ አካባቢዎች በጉድጓድ ውሃ ማልማት መጀመሩና መሬት ጾም እንዳያድር መደረጉም ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጉን አያይዘው ገልጸዋል። የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማሳካትም ለክህሎት መር ስልጠና እንዲሁም የከተማና የገጠር የልማት አቅምችን ወደ ውጤት መቀየር ላይ በቅንጅት መሰራቱን አስረድተዋል። የገጠርና የከተማ ኮሪደር ልማቶች ኢኮኖሚና ማህበራዊ ፋይዳቸውን ለማጉላትም ትኩረት ተሰጥቶ መሰራቱን ጠቅሰዋል።፡ መንግስታዊ አገልግሎት አሰጣጥን ለማቀላጠፍ ወደ ሥራ የገቡ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎቶች ቀደም ሲል ከአገልግሎት ጋር በተያያዘ የሚታዩ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት አስችሏል ብለዋል፡፡ በተከናወኑ ሥራዎች በሁሉም ዘርፍ የተመዘገበው ውጤት አመራሩ ተናቦ በቁርጠኝነት ከሰራ ያቀዱትን ማሳካት እንደሚቻል ማሳያ ነው ብለዋል። በግምገማ መድረኩ የክልል፣ የዞንና የወረዳ አመራሮች የተገኙ ሲሆን የበጀት ዓመቱ የፓርቲና የመንግስት ዕቅድ አፈጻፀም ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል።
ኢትዮጵያን አሸናፊ እናድርግ- እናት ሙዶ አኮ
Jul 15, 2026 364
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ከደቡብ ኦሞ ዞን ሐመር ወረዳ የካራ ማህበረሰብ ተወካይ እና የሰላም እናት ሙዶ አኮ በሀገራዊ የምክክር የመክፈቻ ጉባኤ ላይ ኢትዮጵያን አሸናፊ እናድርግ ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ተካሂዷል። በመክፈቻ ጉባኤው ከደቡብ ኦሞ ዞን ሐመር ወረዳ የመጡት የካራ ማህበረሰብ ተወካይ እና የሰላም እናት ሙዶ አኮ፣ በዚሁ ወቅት መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። እናት ሙዶ የኢትዮጵያ ሴቶች እና እናቶች ለዘመናት በታሪክ ሂደት ውስጥ ተሳትፏቸው የነበረው በደልን በመቀበል እና ሀዘንን በመጋራት ብቻ እንደነበር አስታውሰዋል። በዚህም እናቶች ለዘመናት በሰላም እጦት የደረሰባቸውን መከራ በንግግራቸው ጠቅሰዋል። ዛሬ ግን ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ድምጻቸውን ለመስማት በመጥራቷ የኢትዮጵያ ሴቶችን ድምጽ በመወከል፣ ታሪካዊውን የምክክር መድረክ በክብር መቀላቀላቸውንም በደስታ ተናግረዋል። በዚህም በኢትዮጵያ ያላቸውን ተስፋ እና ሙሉ እምነት አንጸባርቀዋል። እናት ሙዶ አኮ፣ ሀገሪቱ ያሳለፈችው ፈታኝ ጊዜ የጋራ መግባባት በመጥፋቱ እንደሆነ በማሳየት ለነገ የምንተወው ተስፋ መሠረቱ የዛሬው መደማመጥ ብቻ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የሁላችንም የጋራ መኖሪያ እንደሆነች ያነሱት እናት ሙዶ፣ በልባችን የያዝነውን የቀድሞ ቁጣ እና የቂም ቋጠሮ በመፍታት፣ ተመካካሪዎች በሙሉ ለሀገራዊ ለውጥ በጋራ እንዲቆሙ ጥሪ አቅርበዋል። ማን ያሸንፋል ከሚል አስተሳሰብ በመውጣትም፣ ኢትዮጵያን አሸናፊ በሚያደርግ የጋራ ዓላማ ዙሪያ መሰለፍ እንደሚገባ በአጽንኦት ገልጸዋል። የምክክር መድረኩ ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እና ብልፅግና ቁልፍ ምዕራፍ እንደሚሆንም ተናግረዋል። በመድረኩ ኢትዮጵያን አሸናፊ እናድርግ ያሉት እናት ሙዶ፥ የነገዋን ብሩህ ኢትዮጵያ የመገንባት ትልቅ አደራችንን እንወጣ ብለዋል።
የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የአፍሪካ ቀንድን ወደ ብሩህ ተስፋ የሚመራ አይነተኛ እርምጃ ነው -የኢጋድ ዋና ፀሐፊ
Jul 15, 2026 461
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ መላውን የአፍሪካ ቀንድ ቀጣና ወደ ብሩህ ተስፋ የሚመራ አይነተኛ እርምጃ መሆኑን የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ዛሬ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት በዓለም ታሪክ ውስጥ በግጭት የተገነባም ሆነ ያተረፈ ሀገር አለመኖሩን በመጥቀስ፣ የኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና ልማት ሊረጋገጥ የሚችለው በሰላማዊ ውይይትና በመደማመጥ ብቻ እንደሆነ አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ ማንነቷን የምትፈልግ አዲስ ሀገር ሳትሆን፣ ከጥንታዊና ጠንካራ ስልጣኔዎች አንዷ መሆኗን ጠቁመዋል። በታሪካችን፣ በባህላችንና በእምነታችን ውስጥ በርካታ ባህላዊ የእርቅ ስርዓቶች ስላሉ፣ ኢትዮጵያ የራሷን ቁስል የምታክምበት ቁልፍ በእጇ ላይ መሆኑንና መፍትሔ ፍለጋ ወደ ውጭ ማማተር እንደማያስፈልጋት አጽንኦት ሰጥተዋል። በፖለቲካዊ ሕይወት ውስጥ በአስተዳደር፣ በሀብት ክፍፍልና በውክልና ዙሪያ የተለያዩ አመለካከቶች መኖራቸው ሙሉ በሙሉ ተፈጥሯዊና የተለመደ ነው ብለዋል። እነዚህን ልዩነቶች በኃይል ለመፍታት መሞከር ግን መሠረታዊ ስህተት መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ እናቶች፣ አባቶች፣ ወጣቶችና ህጻናት ዛሬ የተወካዮቻቸውን መድረክ እየተመለከቱ ያሉት በጉጉትና በታላቅ ተስፋ እንደሆነ በማንሳት የግጭት አዙሪት በሀገሪቱ ማብቃት እንዳለበት ገልጸዋል። ልዩነቶችን በውይይትና በጋራ መከባበር መፍታት እንደምንችል ለራሳችንና ለዓለም የምናስመሰክርበት መድረክ ነው ብለዋል። የምክክር ጉባኤው ተሳታፊዎች ይህንን ታሪካዊ ዕድል በአግባቡ በመጠቀም በአስተውሎት እንዲመካከሩ በመጠቆም፥ ኢጋድ በዚህ አስደናቂና ታሪካዊ የሰላም ጉዞ ውስጥ ከኢትዮጵያ ጎን በጽናት እንደሚቆም አረጋግጠዋል።
ኢትዮጵያ በኢትዮጵያውያን ለነገ እንድትሆን ሆና ልትገነባ ተሰባስባለች-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Jul 15, 2026 543
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በኢትዮጵያውያን ለነገ እንድትሆን ሆና ልትገነባ ተሰባስባለች ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ተናገሩ፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ባስተላለፉት መልእክት ልሂቃን በሚፈጥሩት ግጭት ሕዝባችን ቢታመስም ባህላችን ግን ለምክክር ያደላ ነበር ብለዋል፡፡ ቤታችን፣ ሞሰባችን፣ አቀማመጣችን፣ ማብሰያችን፣ ወዘተ ክብ ናቸው። ይሄውም ነገርን ሰብሰብ ብሎ በመመካከር ለመከወን እንዲያመች የተሠራ ነው። ክብ መነሻና መድረሻ የለውም። ሩቅና ቅርብ የለውም። ወጪና ገቢ የለውም። ሁሉንም በእኩልነት ያሳትፋል ሲሉ ገልፀዋል። ይሄንን የተረሳ ባህላችንን ወደ ሀገራዊ ምክክር አምጥተነዋል። ኢትዮጵያውያን ከአራቱም ማዕዘን መጥተው በጋራ ይመክራሉ። እሺ በጄ ያለ ሁሉ ዕድል ተሰጥቶታል። እነሆ ኢትዮጵያ በኢትዮጵያውያን ለነገ እንድትሆን ሆና ልትገነባ ተሰባስባለች ብለዋል ። የሀገር ጸሎት ልብና ጆሮ ከእናንተ ጋራ ነው ሲሉም መልእክት አስተላልፈዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከአውሮፓ ሕብረት የውጭ ጉዳይና ደህንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይ ጋር ተወያዩ
Jul 15, 2026 502
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከአውሮፓ ሕብረት የውጭ ጉዳይና ደህንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይ ካያ ካላስ ጋር ተወያይተዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ የአውሮፓ ሕብረት የውጭ ጉዳይና የደህንነት ፖሊሲ ከፍተኛ ተወካይ ካያ ካላስን ዛሬ ተቀብዬ ፍሬያማ ውይይት አድርገናል ብለዋል። በውይይታቸውም በአውሮፓ ሕብረት እና አፍሪካ መካከል ያለውን ግንኙነት ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መምከራቸውን ጠቅሰዋል፡፡ በጋራ ጥቅሞች እና ቅድሚያ በሚሰጣቸው ቁልፍ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሃሳብ ተለዋውጠናል ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ። ትኩረት የሚሹና ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ መሰረት ባደረገው ውይይት ኢኮኖሚያዊ ትብብርን ይበልጥ ለማሳደግና ለማስፋፋት በሚያስችሉ መንገዶች ላይ መምከራቸውንም ጠቁመዋል፡፡
ሀገራዊ ምክክሩ ኢትዮጵያን በጋራ ለመገንባት የሚያስችል ታሪካዊ አጋጣሚ ነው
Jul 15, 2026 415
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ሀገራዊ ምክክሩ የወደፊት የጋራ ኢትዮጵያን የምንገነባበት ታሪካዊ መድረክ ነው ሲሉ የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አሕመድ ሁሴን ገለፁ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ተካሂዷል፡፡ የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ፕሬዚዳንት አሕመድ ሁሴን በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ አሁን የተደረሰበት የምክክር ምዕራፍ በበርካታ ባለድርሻ አካላትና ሀገር ወዳድ ዜጎች ከፍተኛ ልፋት፣ ድካምና መስዋዕትነት የተገኘ ነው። በመሆኑም ሂደቱን በመምራት እዚህ እንዲደርስ ላደረገው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን፣ ለኮሚሽነሮቹና ለመንግስት ምስጋና አቅርበዋል። ዛሬ የተጀመረው ምክክር የወደፊት የጋራ ኢትዮጵያ የሚገነባበት ትልቅ መድረክ መሆኑንም ጠቅሰዋል፡፡ ተመካካሪዎች በተመረጡት አጀንዳዎች ላይ የዜጎችን እውነተኛ ፍላጎትና ተስፋ መሰረት አድርገው በመምከር ዘላቂ መፍትሄ እንደሚያመጡ ሙሉ እምነት እንዳላቸው ገልጸዋል። የሲቪል ማህበራት ለፖለቲካ ያልወገኑና ለትርፍ ያልተቋቋሙ በመሆናቸው በመሃል መንገድ በመቆም የመተማመን ድልድይ የመገንባት፣ የተገለሉ ድምጾችን የማሰማትና የሰላማዊ ምክክር ባህልን የማጠናከር ልዩ ኃላፊነት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ይህ ታሪካዊ ሂደት ስኬታማ ሆኖ እንዲጠናቀቅ እያንዳንዱ ዜጋና ባለድርሻ አካል በባለቤትነት ስሜት እንዲሳተፍ ሂደቱንም በጽኑ እንዲጠብቅ ጥሪ አቅርበዋል።
ሀገራዊ ምክክሩ የፖለቲካ ስልጣን በኃይል ሳይሆን በህዝብ ፍላጎት ብቻ የሚገኝበትን ስልጡን ስርዓት ለመገንባት መሰረተ የሚጣልበት ነው
Jul 15, 2026 226
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር የፖለቲካ ስልጣን በጠመንጃ ሳይሆን በሰለጠነ የፖለቲካ ባህልና በህዝብ ፍላጎት ብቻ የሚገኝበትን ስርዓት ለመገንባት መሰረት የሚጣልበት ነው ሲሉ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ሰለሞን አየለ ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በይፋ ተጀምሯል። በዚሁ መድረክ ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ሰለሞን አየለ እንደተናገሩት፤ ጉባኤው ታሪካዊና ትልቅ ተስፋ የተጣለበት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝቦች በጉጉት ሲጠብቁት የነበረውን ይህን ጉባኤ የዚህ ዘመን ትውልድ እውን እንዳደረገው ጠቅሰዋል። ጉባኤው የፖለቲካ ስልጣን በጠመንጃ ሳይሆን በሰለጠነ የፖለቲካ ባህልና በህዝብ ፍላጎት የሚገኝበትን ስርዓት ለመገንባት መሰረት የሚጣልበት መድረክ ነው ሲሉም ጠቅሰዋል። ሀገሪቱን ከግጭት አዙሪት በማውጣት፣ የፖለቲካ ልዩነቶችን በውይይት መፍታት የሚያስችል ባህል ለመገንባት የሚደረግ ትልቅ ጉዞ መሆኑንም ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት በሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ መግባባትን መፍጠርና በሰላማዊ የፖለቲካ ትግል ሀገርን ከማጽናት አንጻር በርካታ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል ብለዋል፡፡ ሀገራዊ ምክክር የፖለቲካ ልዩነቶችን በጠረጴዛ ዙሪያ መፍትሄ መፈለጊያ፣ የሰላም ግንባታ መሳሪያና የፖለቲካ ሽግግር ማሳለጫ መሆኑን አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት እና አባል የፖለቲካ ድርጅቶች ዛሬ ላይ የተጀመረው ሀገራዊ ምክክር የተሳካ እንዲሆንና የሀገራዊ ምክክሩ ሂደት ሙሉ ለሙሉ እስኪጠናቀቅ ድረስ የበኩላቸውን ሚና እንደሚወጡም አረጋግጠዋል።
ኢትዮጵያ በውጭ ፕሮፓጋንዳ ተጠምዳ ጥቅሟን አሳልፋ ትሰጣለች ብሎ መገመት ከንቱ ምኞት ነው
Jul 15, 2026 322
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ)፦ ለሺህ ዓመታት ጸንታና በቀላሉ በማይበጠስ ጠንካራ ትስስር ተሰናስላ የኖረችው ኢትዮጵያ በውጭ ፕሮፓጋንዳ ተጠምዳ ጥቅሟን አሳልፋ ትሰጣለች ብሎ መገመት ከንቱ ምኞት መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በይፋ ተጀምሯል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፣ ኢትዮጵያ ታሪክ ጠገብና ጥንታዊ ሀገር መሆኗን አስታውሰው፣ በውስጥ የሚከሰቱ ችግሮች በሙሉ እኛው ጀምረን እኛው የምንጨርሳቸው ብቻ እንዳልሆኑ ገልጸዋል። በሀገሪቱ ውስጥ ኮሽ ሲል የሚነቁና የዘመናት ያልተቋረጠ የጠላትነት ታሪክ ያላቸው ኃይሎች መኖራቸውን ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ስትገነባ የማይታዩ፣ ነገር ግን አለመግባባቶች ሲፈጠሩ ጣልቃ የሚገቡ ጊዜ ጠባቂ ኃይሎች መኖራቸውን ጠቅሰው፣ በቅርቡ ቀይ ባሕርን ያጣንበት አጋጣሚ የዚህ እኩይ ታሪካዊ ክስተት የእኛን ስንፍና የመጠቀምና የጣልቃ ገብነት አንዱ መገለጫ መሆኑን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለሺህ ዘመናት ያስተዳደረችውን፣ በባለቤትነት የያዘችውንና ለራሷም ሆነ ለአካባቢው መጠቀሚያ ያደረገችውን ቀይ ባሕር፣ ያልተመረጠ፣ ያልተወያየ መንግሥት በሸፍጥ ኢትዮጵያን የጂኦግራፊ እስረኛ እንድትሆን ማድረጉን አስታውሰዋል። ይህ የሆነበት ዋናው ምክንያት የኢትዮጵያን ብሔራዊ መሻትና ጥቅም ማስቆም የሚችል ኃይል ስለነበረ፣ ስላለና ስለሚኖር ሳይሆን በውስጥ ስንፍናችን በተፈጠረ ድክመት ነው ብለዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ሲገነባ፣ ከተሞች ሲያሸበርቁና ሌሎች የልማት ሥራዎች ሲጀመሩ አብረው ያልነበሩ ኃይሎች፣ ኢትዮጵያውያን እርስ በርስ ሲጨቃጨቁና የውስጥ ችግሮች ሲፈጠሩ ግን ገንዘብ፣ መሣሪያና የሚዲያ ፕሮፓጋንዳ ሲያቀብሉ እንደሚታዩም ጠቁመዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የኢትዮጵያ ሕዝብ በማንኛውም የውስጥ ጉዳይ ላይ ቢለያይና ቢከራከር እንኳን፣ ጉዳዮችን በውይይት መድረኮች መፍታት እንደሚቻል አስገንዝበዋል። በውስጥ ጉዳይ ላይ መከራከርና መወያየት መብት መሆኑን ገልጸው፤ ለሌሎች ኃይሎች ጥቅም ሲባል የኢትዮጵያን ብሔራዊ ፍላጎት አሳልፎ የሚሰጥ "እንክርዳድ" መሆን እንደማይገባና ሁሉም ዜጋ በንቃት እንዲሠራ አጽንኦት ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ ሰማይ ላይ ለሚያንዣብቡ አሞሮች ሲሉ ለገለጿቸው የውጭ ኃይሎች ጠንከር ያለ መልዕክትም አስተላልፈዋል። ከብቱን መርጠን የምንገዛው፣ የቅርጫውንም ባለቤት የምንወስነው እኛ ነን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ኢትዮጵያ ካልተረፋትና በራሷ ፈቃድ ካልሰጠች በቀር፣ አሁን በሚነዛ የውጭ ፕሮፓጋንዳ ተዘናግታ ብሔራዊ ጥቅሟን አሳልፋ ትሰጣለች ብሎ መገመት ፈጽሞ ከንቱ ምኞት መሆኑን አስገንዝበዋል። የውጭ ኃይሎች ለሺህ ዓመታት ጸንታ የኖረችውና በቀላሉ በማይበጠስ ጠንካራ ትስስር ተሰናስላ የኖረችውን ሀገር ታሪክ በትክክለኛው መንገድ በመረዳት፣ ወደ ቀልባቸው ተመልሰው ለጋራ ጥቅም በጋራ እንዲሠሩ ጥሪ አቅርበዋል። ኢትዮጵያ መከራዎችን አልፋ እንድትጸና ያደረጋት ያላት የችግር መፍቻ ሀብት መሆኑንና ኢትዮጵያውያን ከተደማመጡና ከተመካከሩ ሀገር ማጽናት እንደሚቻል ገልጸው፤ ምክክሩ ስኬታማ የሚሆነው የጋራ መፍትሔ ሲገኝ ብቻ እንደሆነ አስረድተዋል። ኢትዮጵያ አራት ሺህ ተመካካሪዎችን በመሰብሰብ ሁሉን አቀፍ ምክክር መጀመሯን ገልጸው፤ ተመካካሪዎች ውጤታማ እንዲሆኑ በጉባኤው አዳራሽ ውስጥ ልባቸውንና አዕምሯቸውን ሰብስበው ሌላውን ወገን ማዳመጥ እንደሚኖርባቸው ተናግረዋል። ምክክሩ ከአዳራሹ ወጥቶ እንደ ፀሐይ ለመላው ኢትዮጵያ እንዲያበራና ለተተኪው ትውልድ የጸናች ሀገርን ለማስረከብ እንዲያስችል ሁሉም ዜጋ በጎ አሻራ እንዲያሳርፍ ጥሪ አቅርበዋል።
ሀገራዊ ምክክሩ ኢትዮጵያ በገዛ እጇ አዲስ ታሪክ ለመጻፍ የሚያስችላትን “ብዕርና ብራና” ያገኘችበት ታሪካዊ አጋጣሚ ነው
Jul 15, 2026 281
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገራዊ የምክክር ሂደቱ ኢትዮጵያ በገዛ እጇ አዲስ ታሪክ ለመጻፍ የሚያስችላትን “ብዕርና ብራና” ያገኘችበት ታሪካዊ አጋጣሚ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ሀገራዊ ምክክሩ በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ ግዙፍና ታላቅ ዓላማ ያለው መሆኑንም ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት፤ በዚህ ታሪካዊ ሀገራዊ ምክክር የማስጀመሪያ ሥነ-ሥርዓት ላይ ለመታደም በመታደሌ ታላቅ ኩራት ይሰማኛል ብለዋል። በሚቀጥሉት ሳምንታት አራት ሺህ ተሳታፊዎችን በአንድ ጣሪያ ስር የሚያሰባስበው ይህ ታላቅ ጉባኤ፣ ኢትዮጵያ በገዛ እጇ አዲስ ታሪክ ለመጻፍ የሚያስችላትን “ብዕርና ብራና” ያገኘችበት ታሪካዊ አጋጣሚ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ጉዞ በኃይለ ቃል ጀምሮ በኃይለ እርምጃ የሚደመደምበትን አዙሪት ሰብረን በንግግርና በውይይት የምንተካበት ወቅት ላይ እንገኛለን ሲሉ ተናግረዋል። ለዚህ ታላቅ ጉዞ መሳካት ላበረከቱት አስተዋጽኦ ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ኮሚሽነሮች ያለኝን ታላቅ ምስጋና ለማቅረብ እወዳለሁ ብለዋል። በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን በማሳተፍ ከሥር ወደ ላይ በዘለቀው አጀንዳ የማሰባሰብ ሂደት ላይ የተመሰረተው ይህ ጉባኤ፣ በቀላሉ የማይደገም እና በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ ግዙፍና ታላቅ ዓላማ ያለው መሆኑን አስገዝንዘዋል። በዚህም ፈተናዎቻችንን ወደ መልካም አጋጣሚዎች በመቀየር ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር ባህልን እናጸናለን ሲሉ ገልጸዋል። በዛሬው ዕለት ለቀጣዩ ትውልድ የሚተርፍ መልካም ዘሮችን እንዘራለን፤ ከሚያፈራውም ፍሬ ልጆቻችን መጠቀም እንዲችሉ እናደርጋለን ነው ያሉት። በዚህ ምክክር ላይ ስንሳተፍ ከየሰፈራችን ወጥተን ለኢትዮጵያ ስንመክር፣ ለልጆቻችን ስንልና እነርሱን እያሰብን ስንወያይ ውጤቱ እጅግ ፍሬያማ እንደሚሆንም ነው የገለጹት። አብረን ተስፋን፣ ይቅርታን እና በጋራ መኖርን እንትከል፤ በሀገር ውስጥ በሚደረግ ውይይትና ይቅርታ ችግሮቻችንን በመፍታት ሀገራችንን ከውጭ ጣልቃ ገብነት እንጠብቅ በማለት አሳስበዋል። ተሳታፊዎች በሙሉ ለኢትዮጵያ መልካም፣ ለአፍሪካ አስተማሪ፣ ለመላው ኢትዮጵያውያን ደግሞ እውነተኛ እረፍትን የሚያመጣ ታሪካዊ ውጤት እንዲያስመዘግቡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥሪ አቅርበዋል።
ኢትዮጵያ ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር ዛሬም እንደ ትናንቱ ለአፍሪካ ምሳሌ ሆና ትቀጥላለች - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jul 15, 2026 201
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ ፈተናዎችን ወደ መልካም ዕድል በመቀየር ዛሬም እንደ ትናንቱ ለአፍሪካ ምሳሌ ሆና እንደምትቀጥል ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በመካሄድ ላይ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ኢትዮጵያ ከተጋረጡባት ማዕበልና መከራዎች የምትሸሽ ሳትሆን፣ ፈተና እና መከራዎችን በጽናት አልፋ ወደ ዕድል የመቀየር የታሪክና ልምድ ያላት ሀገር መሆኗን አንስተዋል። ኢትዮጵያ ትበለፅጋለች ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ፈተናዎችን አልፋ ዛሬም እንደ ትናንቱ ለአፍሪካ ምሳሌነቷን አስከብራ እንደምትቀጥል ገልጸዋል። የጀመርናቸውን መልካም ዘሮች እንዘራለን፣ እንንከባከባለን፣ ዛፍም እናደርጋቸዋለን ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የእነዚህን መልካም ሥራዎችና የልማት ፍሬዎች ዛሬ ላይ ያሉት ሳይሆኑ፣ መጪው አዲስ ትውልድ እንዲጠቀምባቸው ታስቦ እየተሠራ መሆኑን አስገንዝበዋል። ኢትዮጵያ በዚህ የምክክር ጉባኤ በተወከሉ ተመካካሪዎች ለትውልድ የሚበጅና ዘላቂነት ያለው ሐሳብ እንድታመነጭ እያንዳንዱ ዜጋ የበኩሉን ኃላፊነት እንዲወጣም ጥሪ አቅርበዋል።
ሀገራዊ የምክክር ሂደቱ ኢትዮጵያ ለመድረስ ያለመችበትን ግብ የምታሳካበት ታላቅ ዕድል ነው - ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ
Jul 15, 2026 197
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገራዊ የምክክር ሂደቱ ኢትዮጵያ ያስቀመጠቻቸውን ግቦች ማሳካት የሚያስችል ታላቅ ዕድል መሆኑን የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት እና የአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ቺፍ ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ጉባኤ መክፈቻ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬሽን ማዕከል እየተካሄደ ይገኛል። የቀድሞው የናይጄሪያ ፕሬዚዳንት እና የአፍሪካ ህብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ መልዕክተኛ ቺፍ ኦሊሴጉን ኦባሳንጆ ፤ ዛሬ የተጀመረው ሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለቀጣናው እና ለአፍሪካ ታሪካዊ የሚባል ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ እና ናይጄሪያ የውስጥ ችግሮቻቸውን በውይይት እና በንግግር ለመፍታት የመረጡት መንገድ እንደሚያመሳስላቸውም ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በዚህ ታሪካዊ እጥፋት ላይ ሆኖ ያከናወናቸውን ተግባራትና ዝግጅቶች አድንቀዋል። ኦባሳንጆ የምክክር ኮሚሽኑን የመጎብኘት እድል እንዳገኙና በተመለከቷቸው ነገሮች መደሰታቸውን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ህዝቧ፣ የተፈጥሮ ሀብቷ እና የኢኮኖሚ ዘርፉን ጨምሮ በርካታ እድሎች እና አማራጮች ያላት ሀገር መሆኗንም አመልክተዋል። ስንዴ ከውጭ ማስገባት አቁማ ምርት በራሷ አቅም ከማምረት ባለፈ ወደ ውጭ እስከ መላክ መድረሷን ጠቅሰው ይህም የአፍሪካ የምግብ ቅርጫት እንድትሆን የሚያስችላት ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ለማደግ እና ለመለወጥ በርካታ አቅሞች አሏትም ነው ያሉት በመልዕክታቸው። ኢትዮጵያ ትልሞቿ እና ውጥኖቿን እውን ለማድረግ የተሳካ ሀገራዊ የምክክር ሂደት ማከናወን እንደሚጠበቅባት አመልክተዋል። ሀገራዊ ምክክሩ ለኢትዮጵያ የወደፊት ግቦች መሳካት ጉልህ አበርክቶ እንዳለው ጠቅሰው ይህም በአፍሪካ እና በዓለም ደረጃ ያላትን የመሪነት ሚና እንደሚያሳድገው ገልጸዋል።
ሀገራዊ ምክክሩ በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ በእጅጉ የገዘፈ ዓላማ እና ተግባር ያለው ነው
Jul 15, 2026 110
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ምክክሩ በቀላሉ የማይደገም በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ እጅግ የገዘፈ ዓላማና ተግባር ያለው መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ታሪካዊው የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት መካሄድ ጀምሯል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ ጉባኤው በቀላሉ የማይደገም፣ በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ በእጅጉ የገዘፈ ዓላማ እና ተግባር ያለው ነው። ታሪካዊው የሀገራዊ ምክክር መድረክ ለአፍሪካ በብዙ ምሳሌ የሚሆን ሁሉን አቀፍ መድረክ መሆኑን ጠቅሰዋል። መድረኩ ልባም ለሆኑ ሰዎች ትልቅ ዕድል መሆኑን ጠቁመው፤ ይህ መድረክ በታላቅ አክብሮት መከናወን እንደሚገባው ተናግረዋል። ኢትዮጵያውያን ብዙ መከራዎችን አሳልፈዋል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ምክክር ዘላቂ መፍትሔ የሚያመጣ መሆኑን ገልጸዋል። መጪው ትውልድ ዘመኑ እንዲያምር ምክክሩ መልካም አጋጣሚ መሆኑን ገልጸው፤ ይህንን መጠቀም እንደሚገባ አመላክተዋል። ምክክሩ እንደ ታላቅ ዕድል እና መሠረት የሚታይ መሆኑን ጠቁመው፤ የተፈጠረውን ዕድል ለመጠቀም የምንተጋ መሆን አለብን ብለዋል። ተመካካሪዎች ለኢትዮጵያ መምከር እንዳለባቸው ገልጸው፤ መልካም መሠረት ማኖር እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የሀገራችንን የወደፊት ዕጣ ፈንታ በመደማመጥና በመተማመን ላይ መገንባት እንደሚገባም ገልጸዋል።
ልዩነቶችን በምክክር መፍታት ለኢትዮጵያ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ ይከፍታል - ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር)
Jul 15, 2026 117
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ልዩነቶችን በምክክር መፍታት ለኢትዮጵያ አዲስ የታሪክ ምዕራፍ እንደሚከፍት የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለስልጣን (ኢጋድ) ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በመካሄድ ላይ ነው። የምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት (ኢጋድ) ዋና ጸሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ይህ ታሪካዊ የምክክር ጉባኤ በኢትዮጵያ ረዥምና ኩሩ ታሪክ ውስጥ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ወሳኝ ክስተትና ቀኑም ለሀገሪቷ ታሪካዊ ነው። በዓለም ታሪክ ውስጥ በግጭት የተሠራ፣ የተገነባ ወይም ያተረፈ ሀገር አለመኖሩን በአጽንኦት ገልጸዋል። ዛሬ የተሻለ ደረጃ ላይ የደረሱ ሀገራት ስኬታማ ሊሆኑ የቻሉት ሀገራዊ ጥቅማቸውን በማስቀደም፣ በመደማመጥና በመነጋገር መሆኑን ጠቅሰው፤ ልዩነቶች መፈታት የሚችሉት በሰላማዊ መንገድና በውይይት ብቻ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ማንነቷን የምትፈልግ አዲስ ሀገር ሳትሆን በምድር ላይ ካሉ ጥንታዊና ጠንካራ ሥልጣኔዎች መካከል አንዷ መሆኗን የገለጹት ዋና ጸሐፊው፤ በታሪክ፣ በባህልና በእምነት ውስጥ ጥልቅና ውብ የሆኑ የእርቅና የማስታረቅ ሥርዓቶች እንዳሉ አስታውሰዋል። ጥንታዊ የሀገር ባህል ችግር መፍቻ መፍትሔዎች ኢትዮጵያ የራሷን ቁስል የምታክምባቸው ቁልፍ መሣሪያዎች ናቸው ብለዋል። ለችግሮች መፍትሔ ወደ ውጭ ማማተር አያስፈልግም ያሉት ዋና ጸሐፊው፤ ትኩረት ሊደረግ የሚገባው በሀገር ውስጥ ባሉ በርካታ አዎንታዊና አርአያነት ያላቸው ምሳሌዎች ላይ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያውያን ልዩነቶቻቸውን በምክክርና በጋራ መከባበር መፍታት እንደሚችሉ በተግባር የምናስመሰክርበት መድረክ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ታሪክ ወደፊት የሚሠራው በመነጋገር እንደሆነ ገልጸው፤ ተመካካሪዎች ማንኛውንም ጉዳይ በምክክር እንዲፈቱ አደራ ብለዋል። ኢጋድም በዚህ ታሪካዊ ጉዞ ውስጥ ከኢትዮጵያ ጎን በጽናት እንደሚቆም አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ኢትዮጵያ ሰላም እንድታጸናና ሀገር በቀል ሰላማዊ መፍትሄዎች ውጤታማ እንዲሆኑ ያስችላል
Jul 15, 2026 153
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ እየተካሄደ የሚገኘው ይህ ታሪካዊ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ኢትዮጵያ ሰላም እንድታጸናና ሀገር በቀል ሰላማዊ መፍትሄዎች ውጤታማ እንዲሆኑ እንደሚያስችል የአፍሪካ ህብረት ገለጸ። የአፍሪካ ህብረት የኢትዮጵያ ሀገር በቀል ሰላማዊ አማራጮችንና የምክክር ሂደትን መደገፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አመልክቷል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ጉባኤ መክፈቻ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ሴንተር እየተካሄደ ይገኛል። የአፍሪካ ህብረት የፖለቲካ ጉዳዮች፣ የሰላም እና ደህንነት ኮሚሽነር አምባሳደር ባንኮሌ አዶዬ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ይህ ታሪካዊ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ኢትዮጵያ ሰላም እንድታጸናና ሀገር በቀል ሰላማዊ መፍትሄዎች ውጤታማ እንዲሆኑ ያስችላል ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት የኢትዮጵያ ሀገር በቀል ሰላማዊ አማራጮችንና የምክክር ሂደትን መደገፉን አጠናክሮ ይቀጥላልም ብለዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ጅማሮ ታሪካዊ ቀን መሆኑን ጠቁመው የአፍሪካ ህብረት የዚህ ታሪካዊ ሁነት አካል በመሆኑ ኩራት እና ክብር እንደሚሰማው ገልጸዋል። የሀገራዊ ምክክር ጥልቀቱን፣ አሳታፊነቱን፣ አካታችነቱንና ብዝሃነቱን እናደንቃለን ያሉት አምባሳደር ባንኮሌ የአፍሪካ ህብረት ይህን ታሪካዊ ሂደት እንደሚደግፍ አመልክተዋል። ይህ ታሪካዊ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ኢትዮጵያ ሰላም እንድታጸናና ሀገር በቀል ሰላማዊ መፍትሄዎች ውጤታማ እንዲሆኑ ያስችላል ብለዋል። ምክክሩ ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠርና ሰላምና መረጋጋትን በዘላቂነት ለማስፋን ቁልፍ ሚና እንደሚጫወትም ነው የገለጹት። እንደ አፍሪካ የኢትዮጵያ ሰላም፣ መረጋጋትና አንድነት ለቀጣናውና ለመላው አፍሪካ ወሳኝ መሆኑንም አመልክተዋል። የአፍሪካ ህብረት ከ63 ዓመታት በላይ በአዲስ አበባ መቀመጫውን በማድረጉ ክብር እንደሚሰማው ገልጸዋል። አሁንም ሰላምን ለማረጋገጥ፣ ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠርና ዘላቂ ልማት እንዲረጋገጥ እንዲሁም የሁሉም ኢትዮጵያውያን ህልሞች ከአጀንዳ 2063 ጋር እንዲጣጣሙ ህብረቱ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል። በጋራ መግባባት እና መከባበር የሚካሄዱ ሂደቶች ሰላምን ለማምጣት ወሳኝ ሚና እንደሚወጡ ጠቁመዋል።
በኃይለ ቃል ተጀምሮ በኃይል እርምጃ የሚደመደመውን የፖለቲካ ስብራት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማቆም ያስፈልጋል
Jul 15, 2026 149
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ)፦ ፖለቲካችን በኃይለ ቃል ይጀምራል፣ በኃይል እርምጃ ይደመደማል ይህንን ስብራት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ማቆም ያስፈልጋል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በመካሄድ ላይ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማስጀመሪያ መርሃ ግብሩ ባስተላለፉት መልዕክት መከራና ችግር በውስጣቸው ዕድልና መፍትሔ የያዙ ናቸው ብለዋል። ያለፉትን ፈተናዎች በምክክር በመሻገር ለልጆቻችን የተሻለ ሰላም፣ ብልፅግና እና የኑሮ ዘይቤ ለመፍጠር መጣር እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። መንግሥት ባለፉት ዓመታት የተገኙ ዕድሎችን በአግባቡ በመጠቀም በሁሉም ዘርፍ ውጤታማ ሪፎርሞችን ማካሄዱን ጠቅሰው፤ አዲስ አበባም በኮሪደር ልማት ከነበረችበት ቆሻሻ ተላቃ አዲስና ውብ መልክ መያዟን ተናግረዋል። አራት ዓመት የፈጀው አድካሚ ሂደትና ሁሉን አቀፍ የምክክር መድረክ እንዲዘጋጅ ያስፈለገው፣ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የሚታየውን ስብራት ለመጠገን መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እጅግ ታሪክ ጠገብና የሰው ልጅ መገኛ ብትሆንም፣ በፖለቲካ ጉዞዋ ሁልጊዜ በኃይለ ቃል ጀምሮ በኃይል እርምጃ የመደምደም ልምድ መኖሩን አስታውቀዋል። ይህንን የኃይል እርምጃ የታሪካችን አካል የማድረግ የተሳሳተ አካሄድ ለአንዴና ለዘለቄታው ማቆም እንደሚያስፈልግም አጽንኦት ሰጥተዋል። በታሪካችን ውስጥ ስንጨቃጨቅ ጊዜ ጠብቀው እየገቡ መሻቶቻችንን እንዳናሳካ የሚያደርጉ የውጭ ኃይሎች መኖራቸውን በማውሳት፣ በቅርቡ ቀይ ባሕርን ያጣንበት አጋጣሚ የዚህ እኩይ ታሪካዊ ክስተት ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል። እንዲህ ያሉ መጥፎ አጋጣሚዎች እንዳይደገሙና የተፈጠሩ ስብራቶችን ለመጠገን ዛሬ የምናገኛትን እያንዳንዷን ደቂቃ እንደ ታላቅ ዕድል በመቁጠር፣ የኢትዮጵያን ብልፅግና በአስተማማኝ መሠረት ላይ ለመገንባት ሳንታክት መስራት ይገባልም ነው ያሉት።
የተገኘውን ታላቅ የምክክር ዕድል በኃላፊነት ስሜት ልንጠቀምበት ይገባል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 15, 2026 147
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ የተገኘውን ታላቅ የምክክር ዕድል በኃላፊነት ስሜትና በአክብሮት ልንጠቀምበት ይገባል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ጉባዔ ማስጀመሪያ መርሐ ግብር በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል እየተካሄደ ይገኛል፡፡ በመርሐግብሩ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ባስተላለፉት መልዕክት፤ ይህ ጉባዔ በቀላሉ የማይደገም፤ በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ የገዘፈ ዓላማ ያለውና ለአፍሪካ ምሳሌ የሚሆን ሁሉን አቀፍ መድረክ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ አንዳንድ አጋጣሚዎች ያሻችሁን እንድትጽፉ ብዕርና ብራና ያቀብሏችኋል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የዛሬው መድረክም የታሪክ አጋጣሚውን ማዝለቅ ለፈለጉ ሰዎች በዚያ ብዕርና ብራና ላይ ሀገርን የሚገነባ ለዘመናት የሚታወስ ታሪክ ለመጻፍ እድል የሚሰጥ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በተቃራኒው ይህንን እድል የማይጠቀሙ እና ሀገርን ከሚገነባ ይልቅ የሚያፈርስ ታሪክ ጽፈው የሚያልፉ መኖራቸውንም አንስተዋል፡፡ በመሆኑም ይህ ታሪክ ዛሬ እንደይደገም ምክክሩ በኃላፊነት ስሜትና በታላቅ አክብሮት ሊከናወን እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡ እኛ እና ከእኛ በፊት የነበሩ ሰዎች ያጧቸውን ጉዳዮች ዳግም ልጆቻችን እንዳያጡ በታላቅ ኃላፊነት ልንሰራ ይገባል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በርካታ ችግሮች መኖራቸውን ያነሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህንን ችግር ወደ ዕድል መቀየር ከተቻለ የተሻለ ትውልድ መፍጠር እንደሚቻል ጠቁመዋል፡፡ ይህንን ለማምጣት የምክክሩን መልካም አጋጣሚ ወደ ዕድል መቀየር እንደሚገባም ገልጸዋል፡፡ መሰል ዕድል ሲገኝም በኃላፊነት ስሜት በቅጡ የምንጠቀምበት ከሆነ እድል ደጋግሞ ወደ እኛ ይመጣልም ነው ያሉት፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት የተገኘውን እድል ሁሉ በመጠቀም በኢትዮጵያ የፖለቲካ፤ የኢኮኖሚ እና የወታደራዊ ሪፎርም በማካሄድ በርካታ ውጤቶች መገኘታቸውን በማስታወስ ለዚህም የአዲስ አበባ ከተማን ልማት ለአብነት አንስተዋል፡፡ ዛሬም በምናገኘው እያንዳንዱን እድል በመጠቀም ለኢትዮጵያ ብልጽግና መሰረት ለመጣል እንተጋለን ሲሉም አረጋግጠዋል፡፡
የምክክር ጉባኤው ሀገርን የሚታደግና የሚገነባ ታሪክ ለመጻፍ ታላቅ እድል የሚሰጥ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 15, 2026 160
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018(ኢዜአ)፦ የምክክር ጉባኤው ሀገርን የሚታደግ፣ የሚጠቅም፣ የሚገነባና ለዘመናት የሚታወስ ታሪክ ለመጻፍ እድል የሚሰጥ ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ የመክፈቻ ሥነ ሥርዓት በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በመካሄድ ላይ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልዕክት፤ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤው በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ በስፋቱ፣ በአካሄዱ እና በሚያስገኘው ውጤት ታላቅ ዓላማና ተግባር ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ይህ መድረክ ኢትዮጵያን ለሚወከሉ የተዘጋጀ ሁሉን አቀፍ መድረክ መሆኑን በመጥቀስ፣ አጋጣሚዎች ከታሪክ ብዕርና ብራና ፊት እንደሚያቆሙን ጠቅሰዋል፡፡ ይህ የዛሬው መድረክ ሀገርን የሚታደግና የሚገነባ ታሪክ ለመጻፍ ታላቅ እድል የሚሰጥ እንደሆነም አጽንኦት ሰጥተዋል። ይህንን እድል የማይጠቀሙና ደጋግሞ እንደማይገኝ የማይገነዘቡ አካላት ታሪክ ሲገኝ ሀገርን ከሚገነባ ይልቅ የሚያፈርስ ታሪክ ጽፈው እንደሚያልፉ አስታውሰዋል። ስለሆነም ይህ ታሪካዊ የምክክር ዕድል በቀላሉ የማይገኝና ሊደገም የማይችል በመሆኑ፣ እኛ እና ከዚህ በፊት የነበሩ ሰዎች ያጧቸውን እድሎች ልጆቻችን እንዳያጡ በታላቅ አክብሮት ልንከውነው ይገባል ብለዋል። የምክክሩ ተሳታፊዎች በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜትና በትህትና ለምክክር ጉባኤው መሳካት የድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። #በምክክር_የምትጸና_ሀገር_ኢትዮጵያ
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑን የአራት ዓመታት ጉዞ የሚያሳይ ኤግዚቢሽን ጎበኙ
Jul 15, 2026 245
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና ከፍተኛ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች ከኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አመራሮች ጋር በመሆን፣ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑን የአራት ዓመታት ጉዞ የሚያሳይ ኤግዚቢሽን ጎብኝተዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ጉባዔ ማስጀመሪያ መርሐ ግብር በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል እየተካሄደ ይገኛል፡፡