ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
በጠቅላላ ምርጫው ለሴቶችና ወጣቶች ተጠቃሚነት ለሚሰራ ፓርቲ ድምጽ ለመስጠት ተዘጋጅተናል
Apr 16, 2026 98
ጋምቤላ፤ ሚያዚያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦ በዘንድሮው ጠቅላላ ምርጫ ለሴቶችና ወጣቶች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለሚሰራ የፖለቲካ ፓርቲ ድምጽ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን የጋምቤላ ከተማ ወጣቶች ገለጹ። ወጣቶቹ ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን በመጠቀም ለመራጭነት የሚያበቃቸውን የምርጫ ካርድ እየወሰዱም ይገኛሉ። አስተያየታቸውን ከሰጡ የጋምቤላ ከተማ ወጣቶች መካከል ቤዱና ኡከች፤ እየተቃረበ ባለው 7ኛ ዙር ጠቅላላ ምርጫ በተለይም ለሴቶችና ለወጣቶች ተጠቃሚነት ለሚሰራ የፖለቲካ ፓርቲ ድምጽ ለመስጠት መዘጋጀቷን ተናግራለች። ለዚህም ለመራጭነት የሚያበቃትን ካርድ መውሰዷንና ሌሎች እድሜያቸው ከ18 ዓመት በላይ የሆኑ ወጣቶችም ካርድ እንዲወስዱ እየቀሰቀሰች መሆኗን ጨምራ ገልፃለች። ለሴቶችና ወጣቶች መብትና ጥቅም የሚሰራ ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀቷን የተናገረችው ደግሞ ወጣት ኛጆክ ኮንግ ናት። በምትኖርበት ቀበሌ ወጣቶችና ሴቶች የምርጫ ካርድ በመውሰድ ይጠቅመኛል የሚሉትን ፓርቲ እንዲመርጡ እየሰራች መሆኗንም ገልፃለች። ወጣት ካሰች ታፈሰ በበኩሏ፤ዴሞክራሲያዊ መብቷን ተጠቅማ ይበጀኛል የምትለውን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ቀደም ብላ ለመራጭነት የሚያበቃትን ካርድ ወስዳለች። በምርጫውም ለሴቶችና ወጣቶች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ይሰራል ለምትለው የፖለቲካ ፓርቲ ድምጿን ለመስጠት መዘጋጀቷን ተናግራለች።
የሚበጀንን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ካርድ በመውሰድ ተዘጋጅተናል- ነዋሪዎች
Apr 16, 2026 176
ሰቆጣ ፤ሚያዚያ 8 /2018 (ኢዜአ)፦ ለሀገርና ለህዝብ ይበጃል የምንለውን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ካርድ በመውሰድ ተዘጋጅተናል ሲሉ የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ነዋሪዎች ገለጹ። የብሔረሰብ አስተዳደሩ ነዋሪዎች ለኢዜአ እንደገለፁት፤ ለሀገርና ለህዝብ ይበጃል የሚሉትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ካርድ በመውሰድ ተዘጋጅተዋል። በብሔረሰብ አስተዳደሩ የሰቆጣ ወረዳ ባጊሚላ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር አበራ ዘገዬ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በንቃት ለመሳተፍ የሚያስችላቸውን ካርድ ማውጣታቸውን ተናግረዋል። ምርጫ በዴሞክራሲያዊ መንገድ የመንግስት ስልጣን የሚያዝበት በመሆኑ ይበጀናል ይጠቅመናል ያልነውን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅተናል ብለዋል። ሁሉም መምረጥ የሚችል ዜጋ የመራጭነት ካርድ ሊያወጣ እንደሚገባ የመከሩት አርሶ አደር አበራ የሚበጃቸውን ፓርቲ ለመምረጥ የምርጫውን እለት በጉጉት እየጠበቁ መሆናቸውን ተናግረዋል። በሰሃላ ወረዳ የ01 ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ ጥሩወርቅ ሰርፀ በበኩላቸው፤ የመራጭነት ካርድ በማውጣት የዜግነት ሃላፊነታቸውን ለመወጣት መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ካርዱን ለማውጣትም የአካባቢያቸውን ሴቶች በመቀስቀስና አብሮ በመሄድ በጋራ ማውጣታቸውን ጠቁመው በካርዳቸው የሚፈልጉትን ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅተዋል። የሚፈልጉትን የፖለቲካ ፓርቲ ወደ ስልጣን ለማምጣት ለመራጭነት የሚያበቃቸውን ካርድ ማውጣታቸውን የገለጹት ደግሞ የሰቆጣ ከተማ ነዋሪ የሆኑት አቶ ካሳ አበባው ናቸው። ዴሞክራሲያዊና ሰላማዊ ምርጫ ጠንካራና ሰላማዊ አገር ለመገንባት መሰረት በመሆኑ በምርጫው በንቃት በመሳተፍ የዜግነት ግዴታቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። በቀሪ ቀናትም የምርጫ ካርድ ያላወጣው ነዋሪ ወደ ምርጫ ጣቢያዎች በመሄድ ተመዝግቦ ካርዱን በእጁ መያዝ እንዳለበት አስተያየት ሰጪዎቹ አመልክተዋል። ግንቦት 24/2018 ዓ/ም ለሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ እየተካሄደ ያለው የመራጮች ምዝገባ እስከ ሚያዚያ 14/2018 ዓ/ም መራዘሙ ይታወቃል።
የፖለቲካ ምህዳሩ መስፋት ፓርቲዎች የፖለሲ አማራጫቸውን በነጻና በሰላማዊ መንገድ ለህዝቡ እንዲያስተዋውቁ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Apr 16, 2026 241
ወልቂጤ፤ ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ):-የፖለቲካ ምህዳሩ መስፋት የፖለሲ አማራጫቸውን በነጻና በሰላማዊ መንገድ ለህዝብ ለማስተዋወቅ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን በጉራጌ ዞን የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲ ሃላፊዎች ገለጹ። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢና የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የጉራጌ ዞን አስተባባሪ አቶ ደምስ ገብሬ ለኢዜአ እንደገለጹት አሳታፊ ዴሞክራሲ ሥርዓት መገንባት ፍትሀዊ ምርጫን ለማድረግ ወሳኝ ነው። በጉራጌ ዞን የተፈጠረውን ምቹ የፖለቲካ ምህዳር በመጠቀም ነፃና ሰላማዊ ምርጫ ለማከናወን የፖለቲካ ፓርቲዎች በትብብር እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በእስካሁኑ የምርጫ ሂደት የታዩ ጉድለቶችን ፓርቲዎች በውይይትና በመነጋገር እየፈቱ መሆናቸውን አብራርተዋል። የፖለቲካ መህዳሩ መስፋት ፓርታዎቹ ርዕዮተ ዓለማቸውን እና የተለያዩ ፕሮግራማቸውን ለህዝብ በነጻነት ለማስተዋወቅና ከደጋፊዎቻቸው ጋር ለመምከር ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ገልጸዋል። በዞኑ የፖለቲካ ፓርቲዎች ህጋዊ መንገድን ተከትለው በምርጫው አሸናፊ ለመሆን በነጻነት እየተፎካከሩ መሆናቸውን ያነሱት ደግሞ የጉራጌ ዞን የፖለቲካ ፓርቲዎች ምክር ቤት ምክትል ሰብሳቢና በብልፅግና ፓርቲ የዞኑ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ አለማየሁ ገብረመስቀል ናቸው። ፓርቲያቸው በመጪው ግንቦት ወር የሚካሄደው ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ነፃ፣ ሰላማዊና አሳታፊ እንዲሆን የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል። በሀሳብ የበላይነት ላይ የተመሰረተ ፉክክር እየተደረገ ነው ያሉት አቶ አለማየሁ፣ የተለያዩ መገናኛ ብዙሀንን በመጠቀም የፓርቲውን የፖሊሲ አማራጮች ለህዝብ ማስተዋወቃቸውን ገልጸዋል። ጎጎት ለጉራጌ አንድነት እና ፍትህ ፓርቲ የጉራጌ ዞን ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አብዱልአዚዝ ሙሰማ (ዶ/ር) በበኩላቸው በዘንድር ጠቅላላ ምርጫ የፖለቲካ ምህዳሩ መስፋቱ ተናግረዋል። ይህም እንደፓርቲ ያላቸውን የፖሊሲ አማራጮች በተለያየ መንገድ ለህዝብ በነጻነት ለማቅረብ እንዳስቻለቸው ገልጸው፣ ፓርቲው የዘንድሮ ምርጫ ነጻ፣ ፍትሀዊና ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል። ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎችም ለአገር ይጠቅማል ያሉትን ሀሳብ በሰለጠነ መንገድ እያቀረቡ መሆናቸውን ነው የጠቆሙት። የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሕግን ባከበረ መንገድ ጠንካራ ተሳትፎ ማድረግ ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ይበልጥ እንዲጎለብት መሰረት መሆኑን ተረድተው በእዚሁ አግባብ እየተንቀሳቀሱ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የምርጫ ክርክሩም የሀገርን ብሔራዊ ጥቅምና የዜጎችን ክብር ባስጠበቀ መንገድ እየተካሄደ መሆኑን አስረድተዋል።
በካርዳችን ለሀገርና ለህዝብ የሚበጅ ፓርቲን ለመምረጥ ተዘጋጅተናል- ነዋሪዎች
Apr 16, 2026 222
ጎንደር፤ ሚያዚያ 8/2018 (ኢዜአ)፡-በምርጫ ካርዳችን ለሀገርና ለህዝብ የሚበጅ ፓርቲን ለመመምረጥ ተዘጋጅተናል ሲሉ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ይፋ ባደረገው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት የመራጮች ምዝገባ እየተካሔደ መሆኑ ይታወቃል። ምዝገባው ሚያዝያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም የሚጠናቀቅ ሲሆን ዜጎች በቀሪዎቹ ጥቂት ቀናት ተመዝግበው ካርዳቸውን በመውሰድ የዜግነት ግዴታቸውን መወጣት እንዳለባቸው እየተገለፀ ነው። በጎንደር ከተማ የምርጫ ካርድ በመውሰድ ላይ የነበሩ ዜጎች ለኢዜአ እንዳሉት፤ ዴሞክራሲያዊ መብታችንን በመጠቀም ለቀጣዮቹ አምስት ዓመታት ሀገሪቱን የሚመራ ፓርቲን ለመምረጥ ተዘጋጅተናል። አስተያየት ከሰጡ ነዋሪዎች መካከል አቶ ሃይለማርያም አለሙ፤ "እኔ አካል ጉዳተኛ ብሆንም ይህ ታሪካዊ አጋጣሚ ሊያመልጠኝ አይገባም በማለት በምርጫው እለት ድምፄን ለመስጠት የሚያስችለኝን ካርድ በእጄ ይዣለሁ" ብለዋል። በጠቅላላ ምርጫው ለሕዝብ፣ ለሀገርና በተለይም ለአካል ጉዳተኞች ይበጃል ለምለው ፓርቲ ድምፄን ለመስጠት ተዘጋጅቻለሁ ሲሉም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሃይማኖት አባት የሆኑት መላዕከ ገነት አባ ገብረመስቀል፤ በህዝብ ድምጽ የተመረጠ መንግስት ለመመስረት ምርጫ ማካሔድ ተገቢ በመሆኑ የመራጭነት ካርድ ወስጃለሁ ነው የሚሉት። ምርጫ የሰለጠነ ፖለቲካ መገለጫ በመሆኑም ከግጭትና አለመግባባት በመውጣት በዴሞክራሲያዊ መንገድ ሀገሪቱን የሚያስተዳድሩ አካላትን ወደ ስልጣን ማምጣት ይገባል ነው የሚሉት። ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ ሙሃባው ሽፈራው፤ ለሀገርና ህዝብ የሚጠቅም ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት በምርጫው ጠንካራ ተሳትፎ ማድረግ ይገባል ብለዋል። በሀገር ጉዳይ ምንም ዓይነት ልዩነት ሳይገድበን ለሰላም፣ ለልማትና ዴሞክራሲ መስራት ያለብን ሲሆን በመረጥነው መንግስት ለመተዳደር ከወዲሁ የምርጫ ካርድ መያዝ ይጠበቅብናል ሲሉም ተናግረዋል። የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የድምፅ መስጫ ዕለት ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም መሆኑን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያወጣው መርሃ ግብር ያመለክታል።
የኢትዮጵያና ናይጄሪያ የህግ አውጭዎች ትብብር የዲፕሎማሲያዊና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን ያጠናክራል
Apr 15, 2026 1253
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7/2018 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያና ናይጄሪያ የህግ አውጭዎች ትብብር በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ዲፕሎማሲያዊና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት እንደሚያጠናክር በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዲማ ነገዎ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከናይጄሪያ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከመጡ የፓርላማ አባላት ጋር የልምድ ልውውጥ አድርጓል፡፡ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዲማ ነገዎ (ዶ/ር) የኢትዮጵያን ፓርላማ አወቃቀር፣ የስልጣን ዘመንና ተግባሩን በተመለከተ ለናይጄሪያ ፓርላማ ተወካዮች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ዲማ ነገዎ (ዶ/ር) በማብራሪያቸው፤ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሀገሪቷ ከፍተኛው የህግ አውጭ አካልና አስፈጻሚ አካላትን የሚከታተል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ እንደ አውሮፓውያን የዘመን ቀመር በ1995 የጸደቀው ህገ መንግሥት ኢትዮጵያን ከአሀዳዊ አስተዳደር ስርዓት ወደ ፌደራሊዝም እንድትሸጋገር አድርጓታል ብለዋል፡፡ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በሪፎርም የአሰራር ማሻሻያ በማድረግ በ13 ቋሚ ኮሚቴ የተቋማት አፈፃፀም ጥብቅ ክትትልና ድጋፍ እንደሚደረግበት ገልጸዋል፡፡ የህዝብ ተወካዮች ምክርት ቤት 44 በመቶ ሴቶችን የምክር ቤት አባል መሆናቸውን በመግለጽ፤ መንግስት በመከላከያና በሌሎች ተቋማት ሴቶች እንዲመሩ በማድረግ ቁልፍ ሚና እየተወጣ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያና ናይጄሪያ የፓርላሜንታዊ ስርዓት የሚከተሉ ሀገራት መሆናቸውን ገልጸው፤ በፓን አፍሪካኒዝም መንፈስ የጋራ ዓላማ አላቸው ብለዋል፡፡ ሁለቱ ሀገራት ለአፍሪካ ህብረትና ለአህጉሪቱ አንድነት የጎላ አበርክቶ እንዳላቸው በመጥቀስ፤ ትብብራቸው በመካከላቸው ያለውን ዲፕሎማሲያዊና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት የሚያጠናክር መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በናይጄሪያ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ብሔራዊ ጉባኤ አገልግሎት ኮሚሽን አባልና የልዑካን ቡድኑ መሪ ላዋን ማህሙድ፤ ኢትዮጵያና ናይጄሪያ ብዝሃ ማንነት ያላቸው ሀገሮች መሆናቸውን ገልጸው፤ ውይይቱ ዓለም አቀፋዊ የፓርላሜንታዊ ትብብርን ማጠናከር ያስችላል ብለዋል፡፡ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የሁለትዮሽ ግንኙነት በማጠናከር ዘላቂነት ያለው ዲሞክራሲ ለመገንባት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል፡፡ ኢትዮጵያና ናይጄሪያ ፓርላሜንታዊ ስርዓት የሚከተሉና ብዝሃ ማንነት ያላቸው በመሆናቸው ልምዳቸው አንዳቸው ለአንዳቸው ጠቃሚ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሃብት ልማት ሥራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ(ዶ/ር)፤ በበኩላቸው የኢትዮጵያና ናይጄሪያ ግንኙነት ረጅም ጊዜ ያስቆጠረ ነው ብለዋል፡፡ ሁለቱ ሀገራት በተፈጥሮ ሀብት የበለጸጉ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ የጋራ ተጠቃሚነታቸው ለማረጋገጥ ወሳኝ ግንኙነት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም በሰው ሀብት ልማት፣ በቴክኖሎጂ የዕውቀት ብቻ ሳይሆን የክህሎት፣ የሥራ እና ስታርት አፕ ልምዶችን ይለዋወጣሉ ብለዋል፡፡
ይበጀናል የምንለውን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ካርድ ወስደናል- የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች
Apr 15, 2026 910
ቦንጋ፤ ሚያዚያ 7/2018 (ኢዜአ):-በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ተጠቅመው ይበጀናል ያሉትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ የምርጫ ካርድ መውሰዳቸውን የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በመጪው ግንቦት ወር ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የመራጮች ምዝገባ እስከ ሚያዚያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም እንዲራዘም ማድረጉ የሚታወስ ነው። በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የቦንጋ ከተማ ነዋሪዎች ለመራጭነት የሚያበቃቸውን ካርድ በመያዝ የድምፅ መስጫ ቀንን በመጠባበቅ ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል መምህር መስፍን ማሞ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ የሀገርን ልማትና ሰላም ያስቀጥላል ያሉትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ የሚያበቃቸውን የምርጫ ካርድ እንደወሰዱ ተናግረዋል። ዴሞክራሲያዊ ምርጫ በዜጎች የነቃ ተሳትፎ የሚከናወን በመሆኑ እሳቸውም ምርጫው ስኬታማ እንዲሆን የድርሻቸውን እየተወጡ መሆኑን ገልፀዋል። የሀገርን ልማትና ሰላም ለማስቀጠል የተሻለ ራዕይ ያለውን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ፓርቲዎች በመገናኛ ብዙኃን እያደረጉት ያለውን ክርክርና የሚያቀርቧቸውን የፖሊሲ አማራጮች እየተከታተሉ መሆኑን ተናግረዋል። ሀገርን ለማሻገርና ልማትን ለማጠናከር ዴሞክራሲያዊ ምርጫ ያለውን ጥቅም በአግባቡ በመረዳታቸው ከራሳቸው ባለፈ ሌሎችም የምርጫ ካርድ እንዲወስዱ የበኩላቸውን እየተወጡ መሆኑን የገለጹት ደግሞ አቶ ንጉሴ ገብረሰንበት የተባሉ ሌላው አስተያየት ሰጪ ናቸው። በመጪው ግንቦት ወር በሚካሄድ ምርጫ ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ተጠቅመው ይመራኛል፣ መብቴንም ያስጠብቃል፣ የሀገርንና የአካባቢውንም ልማት ያስቀጥላል ያሉትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ለምርጫው ዴሞክራሲያዊነት በሂደቱ ላይ በንቃት መሳተፍ ወሳኝ ነው ያሉት ደግሞ አቶ ብርሃኑ ኬቶ ናቸው። የምርጫ ሕጉን አክብረው በምርጫው ለመሳተፍ ከመዘጋጀታቸው ባለፈ ሌሎችም የዜጎችን ሕይወት እና ሀገርን የተሻለ ደረጃ ላይ ያደርሳል ላሉት ፓርቲ ድምጻቸውን እንዲሰጡ የማስገንዘብ ሥራ እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። ምርጫ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ መሰረት በመሆኑ ዕድሜው ለመራጭነት የደረሰ ሁሉ የምርጫ ካርድ በመውሰድ የሚበጀውን የፖለቲካ ፓርቲ በነጻነት በመምረጥ መብቱን ሊጠቀም ይገባል ሲሉም አስገንዝበዋል።
ወሎ የብዝኃነት እና የአብሮነት ተምሳሌት ናት - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 15, 2026 1156
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ ወሎ የብዝኃ ሃይማኖትና ባህል መገኛ፣ የፍቅርና የአብሮነት ተምሳሌት እንዲሁም የታሪክ ማህደር ናት ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ወሎ ኮምቦልቻ መግባታቸውን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም፣ እንደ ቦርከና ወንዝ የማይነጥፈው የህዝቡ ገራገርነትና የማይጠገበው ትኅትና፣ እንዲሁም እንደ ጦሳ ተራራ የገዘፈው መስተንግዶና ደማቅ አቀባበል ልባቸውን በሐሴት እንደሞላው ገልጸዋል። በወሎ ኮምቦልቻ አየር ማረፊያ ሲደርሱ ደማቅ አቀባበል ላደረጉላቸውና አርሂቡ ብለው ለተቀበሏቸው ለአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር፣ ለክልሉ ከፍተኛ አመራሮች፣ ለሃይማኖት አባቶች፣ ለሀገር ሽማግሌዎች እና ለመላው የወሎ ሕዝብ ላቅ ያለ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። Ethiopian News Agency #ኢዜአ
የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሰው ኃይል ልማት ፕሮግራም ለኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ስኬት አዲስ ምዕራፍ ይከፍታል
Apr 15, 2026 756
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 7/2018 (ኢዜአ)፦የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሰው ኃይል ልማት ፕሮግራም ለኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ስኬት አዲስ ምዕራፍ እንደሚከፍት ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) አስታወቁ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እየተለወጠ ካለው ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ ሁኔታ ጋር ራሱን እንዲያራምድ፣ ዲፕሎማቶቹም በቂ እውቀትና ክህሎት እንዲኖራቸው ለማድረግ ታስቦ የተዘጋጀ የሰው ኃይል ልማት ፕሮግራም ይፋ ማድረጊያ መርኃ ግብር አካሂዷል። ፕሮግራሙ ዲፕሎማቶች ወቅቱ የሚጠይቀውን በቂ እውቀትና ክህሎት ታጥቀው አገራዊ ጥቅምን ለማስከበር እንዲችሉ ለማድረግ የታለመ ነው። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ (ዶ/ር) በመርኃ ግብሩ ላይ እንደገለጹት፤ ተቋሙን በላቀ ደረጃ ለማዘመን የሚያስችል የሦስት ዓመት አጠቃላይ የተቋም ግንባታ ፍኖተ ካርታ ተነድፎ ወደ ሥራ ተገብቷል። የፍኖተ ካርታው አካል የሆኑ የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን ጠቁመው፤ በተለይም ተቋሙን የማዘመን እና ምቹ የሥራ አካባቢን የመፍጠር ተግባራት በትኩረት እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል። በተቋም ውስጥ ያሉ ባለሙያዎችን አቅም ማላቅ ለውጤታማነት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ፤ ዲፕሎማቶች ውስብስብ በሆነው ዓለም አቀፋዊ ሁኔታ ውስጥ ኢትዮጵያን በብቃት እንዲወክሉ ክህሎት፣ እውቀትና ግንዛቤያቸው አሁን ካለበት በላይ ከፍ እንዲል እንደሚደረግ ተናግረዋል። የሰው ኃይል ልማት ፕሮግራሙ ተለዋዋጭ የሆነውን ዓለም አቀፋዊ የፖለቲካ እና የኢኮኖሚ ሁኔታ ታሳቢ ያደረገ እንደሆነ ገልፀዋል። ሚኒስቴሩ ተቋማዊ አቅምን፣ በውስጣዊ አሠራሩ ዘመናዊ እና ውጤታማ እንዲሆን ማድረግ ቀዳሚ ዓላማው እንደሆነ ገልፀዋል። ዲፕሎማቶች እና የሥራ ኃላፊዎች በሙያዊ ክህሎት፣ በትንታኔ እና በተግባራዊ ዕውቀት እንዲበለጽጉ ማድረግም እንዲሁ። ዓለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ የዲፕሎማሲ ልምዶችን በተቋሙ ውስጥ ተግባራዊ ማድረግን ታሳቢ ያደረገ እንደሆነም ገልፀዋል። የፕሮግራሙ ተግባራዊ መሆን ኢትዮጵያ በቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ ያላትን ተፅዕኖ ፈጣሪነት እንደሚያሳድገው አመልክተው፤ ለሀገሪቷ የዲፕሎማሲ ስኬት አዲስ ምዕራፍ እንደሚከፍት ተናግረዋል። ይህ ሁለገብ የሪፎርም አጀንዳ ለዲፕሎማቶች እና ለሚኒስቴሩ ሠራተኞች የሙያ ሥልጠና መስጠት፣ የውጭ ግንኙነት ኢንስቲትዩት (IFA) ሥርዓተ-ትምህርትን መከለስ፣ አዲስ የሥነ-ምግባር ደንብ ማዘጋጀት እና ከፍተኛ የድህረ-ምረቃ ትምህርቶችን ማመቻቸት የሚሉት ይገኙበታል።
ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመስራት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ
Apr 14, 2026 1859
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የላይቤሪያ ሪፐብሊክ ፕሬዝደንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ ከሁለትዮሽ ስብሰባቸው ቀጥሎ ሁለት የመግባቢያ ስምምነቶች ልውውጥ ላይ ተገኝተዋል። እነዚህ ስምምነቶች በትምህርት፣ በሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፎች ላይ በማተኮር ለወደፊት ትብብራችን እንደ ስትራቴጂካዊ መሠረት እና ተግባራዊ ፍኖተ-ካርታ እንደሚያገለግሉ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት መረጃ ያመላክታል። የትብብር ማዕቀፉ፤ ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያን በመደመር መርህ በማጣመር ለአኅጉራዊ ትስስር ዋነኛ አንቀሳቃሽ ኃይል ከመሆኑም ባለፈ፣ የአፍሪካ ሀገራት በእውነተኛ ትብብር ምን ሊያሳኩ እንደሚችሉ እንደ ታላቅ ተምሳሌት የሚጠቀስ መሆኑም ተገልጿል።
በፈተናዎች ሁሉ የጸናው የኢትዮጵያና የላይቤሪያ ወዳጅነት
Apr 14, 2026 1142
በሙሴ መለሰ ኢትዮጵያና ላይቤሪያ ዘመናትን የተሻገረ ወዳጅነት አላቸው። ይሄ ወዳጅነት በፈተናዎች ጊዜ ሁሉ ጸንቶ የዘለቀም ነው። ሁለቱ ሀገራት በአፍሪካ ውስጥ ብቸኛ ነፃ ሀገራት በመሆናቸው፣ በዓለም አቀፍ መድረኮች (ለምሳሌ በሊግ ኦፍ ኔሽንስ) የአፍሪካውያን ድምፅ ሆነው በጋራ ይቆሙም ነበር። የሀገራቱ የወዳጅነት እና የትብብር ስምምነትም እ.አ.አ በ1950ዎቹ መጨረሻ ላይ የጀመረ ሲሆን፣ በመካከላቸው ያለው ዘላቂ ወዳጅነት እና በዓለም አቀፍ መድረኮች (እንደ ተባበሩት መንግሥታት ድርጅት) በጋራ ለመቆም ቃል የተገባበት ሰነድም ተደርጎ ይወሰዳል። የዘመናዊ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መሠረት የጣሉትም ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ እና ፕሬዝዳንት ዊሊያም ቱብማን ናቸው። እ.ኤ.አ. በ1954 ፕሬዝዳንት ቱብማን ወደ አዲስ አበባ ያደረጉት ጉብኝት በሁለቱ ሀገራት መካከል ይፋዊ ግንኙነት እንዲጀመር በር ከፍቷል። ቀዳማዊ አፄ ኃይለ ሥላሴ እ.አ.አ. 1958 ጉብኝት ወደ ሞንሮቪያ በማድረግ፣ በምዕራብ አፍሪካ የሚገኙ የነፃነት ንቅናቄዎችን በጋራ ለመደገፍ ተወያይተዋል። እነዚህ ጉብኝቶች የሁለትዮሽ ብቻ ሳይሆኑ አህጉራዊ ፋይዳም ነበራቸው። እ.አ.አ በ1963 የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) ሲመሰረት፣ ሁለቱ ሀገራት "የሞንሮቪያ" እና "የካዛብላንካ" ቡድኖችን ልዩነት በውይይት በመፍታት ለአህጉሪቱ አንድነት የጀርባ አጥንት መሆናቸውን አስመስክረዋል። በ1960ዎቹ መጀመሪያ ላይ በ”ሞንሮቪያ ቡድን” እና "የካዛብላንካ ቡድን" መካከል የነበረውን ልዩነት ለማጥበብ ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ በጋራ በመስራታቸው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ሊመሰረት ችሏል። የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት በችግር ውስጥ የተፈተነ ወዳጅነት ነው የሚል ሀሳብ በብዙዎች ይነሳል። የዚህም ምክንያት ኢትዮጵያ በላይቤሪያ የነበራት የሰላም ማስከበር ሚና ነው። ላይቤሪያ ለ14 ዓመታት በዘለቀው አውዳሚ የእርስ በርስ ጦርነት ምክንያት መንግሥታዊ መዋቅሯ ፈርሶ ነበር። እ.ኤ.አ. በ2003 የተፈረመውን የሰላም ስምምነት ተከትሎ፣ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (UN) ሰላም እንዲያስከብሩ ከጠራቸው አገራት መካከል ኢትዮጵያ ቀዳሚዋ ነበረች። ኢትዮጵያ በላይቤሪያ በርካታ ሰራዊቷን በማሰማራት ለሀገሪቷ ሰላም ዋጋ ከፍላለች። ሰራዊቱ አማፂያንን ትጥቅ በማስፈታት፣ ተዋጊዎች ከማህበረሰብ ጋር እንዲቀላቀሉ በማድረግ እና የቀድሞ ታጣቂዎች ወደ ሰላማዊ ህይወት እንዲመለሱ ከፍተኛ ስራ ሰርቷል። ዋና ከተማዋ ሞንሮቪያ እና በገጠራማ አካባቢዎች የተኩስ አቁም ስምምነቱ እንዳይጣስ ጥብቅ ቁጥጥር አድርጓል። የኢትዮጵያ ሰራዊት የጤና ቡድን በየሰፈሩ በመዘዋወር ለላይቤሪያውያን ነፃ የህክምና እርዳታ እና መድሃኒትም ይሰጥ ነበር። ሰራዊቱ የራሱን ስንቅ ለተቸሩ ዜጎች በማካፈል ወንድማማችነትን በተግባር አሳይቷል። እ.ኤ.አ በ2014 የኢቦላ ወረርሽኝ በላይቤሪያ በከፋ ሁኔታ በተከሰተበት ወቅትም፣ ሌሎች ሀገራት ሰራዊታቸውን ሲያስወጡ ኢትዮጵያ ግን የህክምና ቡድኖችን እና ሰራዊቷን በማቆየት ከላይቤሪያ ህዝብ ጎን ቆማች። ኢትዮጵያ በላይቤሪያ ሶስት ተከታታይ ሰላማዊና ዲሞክራሲያዊ ምርጫዎች እንዲካሄዱ በሰላም ማስከበሩ ረገድ ከፍተኛ ሚና ተጫውታለች። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት እና የላይቤሪያ መንግሥት ለኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪዎች የላቀ አገልግሎት ሜዳሊያ እና የምስጋና የምስክር ወረቀት ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ በላይቤሪያ የነበራት የሰላም ማስከበር ሚና ከወታደራዊ ተልዕኮ ባለፈ የደም እና የአጥንት መስዋዕትነት ከፍላለች። ይህ የሰራዊቱ ተሳትፎ ዛሬም ድረስ በሁለቱ ሀገራት ህዝቦች መካከል ላለው ጥብቅ ወዳጅነት ዋነኛው ምክንያት ተደርጎ ይወሳል። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በሀገራቱ መካከል የሚደረጉ የጉብኝት ልውውጦች እና ውይይቶች ለሁለትዮሽ ትብብሩ መጠናከር አስተዋጽኦ አድርገዋል። የቀድሞዋ የላይቤሪያ ፕሬዝዳንት ኤለን ጆንሰን ሰርሊፍ እ.አ.አ በ2006 ስልጣን በያዙ ማግስት አዲስ አበባን ጎብኝተዋል። ይህም ኢትዮጵያ በላይቤሪያ ሰላም ለማስፈን ላደረገችው ድጋፍ እውቅና የሰጡበት ነበር። ሰርሊፍ በላይቤሪያ የተከሰተው የኢቦላ ወረርሽኝ ሲያበቃ እ.አ.አ ጁላይ 2015 ኢትዮጵያን በመጎብኘት ለተደረገላቸው የህክምና ቡድን ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። የቀድሞዋ ፕሬዝዳንት እ.አ.አ በ2017 ለሶስት ቀናት ይፋዊ የስራ ጉብኝት ያደረጉ ሲሆን ከቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳላኝ ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አድርገዋል። ፕሬዝዳንቷ በወቅቱ የሃዋሳ ኢንዱስትሪ ፓርክን የጎበኙ ሲሆን ላይቤሪያ ከኢትዮጵያ የጨርቃ ጨርቅ ልማት ዘርፍ ልምድ መቅሰም እንደምትፈልግ በወቅቱ ገልጸው ነበር። የላይቤሪያ የእግር ኳስ ኮከብ እና የቀድሞው ፕሬዝዳንት ጆርጅ ዊሃ እ.አ.አ በ2018 ስልጣን ከያዙ በኋላ በአዲስ አበባ በተካሄደው 30ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ የተሳተፉ ሲሆን ከጉባኤው ጎን ለጎን ከወቅቱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ ጋር ተገናኝተው በሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ላይ ተወያይተዋል። የቀድሞው የላይቤሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዲ-ማክስዌል ሳህ ከማያህ እ.አ.አ በ2022 በአዲስ አበባ ጉብኝት በማድረግ በሁለቱ ሀገራት መካከል የጋራ የሚኒስትሮች ኮሚሽን (Joint Ministerial Commission) እንዲቋቋም ስምምነት ተፈራርመዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በላይቤሪያ የሰላም ማስከበር ተልዕኮ (UNMIL) ላይ በነበረበት ወቅት፣ የተለያዩ የመከላከያ ሚኒስትሮች እና የጦር አዛዦች የኢትዮጵያን ሰላም አስከባሪ ኃይል ለመጎብኘት እና ከላይቤሪያ ባለስልጣናት ጋር ለመወያየት በተደጋጋሚ ወደ ሞንሮቪያ ተጉዘዋል። ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ በተለያዩ ጊዜያት ባደረጓቸው ውይይቶች በተለያዩ ዘርፎች በትብብር መስራት የሚያስችላቸውን ስምምነቶችም ተፈራርመዋል። ሰላም ፣ ደህንነት፣ ጤና፣ የአየር አገልግሎት፣ የቪዛ ነፃ መብት ፣ የንግድ ትብብር ማዕቀፍ፣ ግብርና፣ ትምህርት፣ ባህል እና ስፖርት ስምምነት ከተደረገባቸው ዘርፎች መካከል ይጠቀሳሉ። የአየር አገልግሎት ስምምነቱ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ሞንሮቪያ ያለምንም ገደብ እንዲበር እና ላይቤሪያን ከቀሪው ዓለም ጋር ማገናኘት የሚያስችል ህጋዊ ማዕቀፍ ነው። የሰላም ማስከበር ስምምነቱ በተባበሩት መንግሥታት ማዕቀፍ ውስጥ የኢትዮጵያ ሰላም አስከባሪ ኃይል እንድትልክ የተደረገው ስምምነት በላይቤሪያ መረጋጋት እንዲመጣ ትልቅ ድርሻ ነበረው። በኪነ-ጥበብ እና በስፖርት ዘርፍ (በተለይም በእግር ኳስ) የሁለቱ ሀገራት ወጣቶች ልምድ እንዲለዋወጡ የሚያስችሉ የመግባቢያ ሰነዶች ተፈርመዋል። የወቅቱ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ቦአከይ እ.አ.አ 2023 ፕሬዝዳንት ሆነው በተመረጡበት ወቅት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የቆየ ግንኙነት ለማደስ እና በንግድ ዘርፍ በጋራ ለመስራት ፍላጎታቸውን ገልጸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በየካቲት ወር 2018 ዓ.ም ከተካሄደው 39ኛው የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ከላይቤሪያ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ቦአካይ ጋር ውይይት አድርገዋል። የሁለትዮሽ ውይይቱ በቴክኖሎጂ፣ በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ እና ኢትዮጵያ ለመገንባት ባቀደችው የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ ዩኒቨርሲቲ ላይ ያተኮረ ነበር። በውይይቶቹ ላይ ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ በንግድ እና ኢንቨስትመንት ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገልጸዋል። የላይቤሪያው ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ ለስራ ጉብኝት ትናንት ማምሻውን አዲስ አበባ ሲገቡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አቀባበል አድርገውላቸዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክትም የላይቤሪያ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ የነገ ብሩህ ተስፋ እየተሰራባት ወደ ምትገኘው ምድረ ቀደምት ኢትዮጵያ እንኳን በሰላም መጡ ብለዋል። በፕሬዝዳንቱ ቆይታ እጅግ ፍሬያማ ውይይት እንደሚኖራቸውም ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። የፕሬዝዳንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ የስራ ጉብኝት የሁለቱን ሀገራት ታሪካዊ ወዳጅነት የበለጠ እንደሚያጠናክርም ታምኖበታል። የኢትዮጵያ እና የላይቤሪያ መጻኢ ግንኙነት ከታሪካዊ ወዳጅነት ወደ ስትራቴጂካዊ የኢኮኖሚ አጋርነት የማሳደግ ፍላጎት በሁለቱም ወገን በኩል አለ። በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው የአቪዬሽን ትስስር፣ የቴክኖሎጂ ልውውጥ እና በአህጉራዊ የነፃ ንግድ ቀጠና (AfCFTA) ማዕቀፍ የሚደረግ ትብብር ለጋራ ብልጽግና መሰረት ይጥላል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከላይቤሪያው ፕሬዝደንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ ጋር ተወያዩ
Apr 14, 2026 1167
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከላይቤሪያ አቻቸው ፕሬዝደንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ ጋር የሁለትዮሽ ውይይት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በመልዕክታቸው ከላይቤሪያው ፕሬዝዳንት ጋር የነበራቸው ውይይት ፍሬያማ እንደነበር አመልክተዋል። በውይይታቸው በተለያዩ ዘርፎች ያላቸውን የቆየ አጋርነት ይበልጥ ለማጠናከርና ለማስፋት ወሳኝ ምዕራፍ መከፈቱን ገልጸዋል። ከሁለትዮሽ ስብሰባው በመቀጠል፣ በሁለቱ ሀገራት በኩል ቅድሚያ የሚሰጣቸውን ጉዳዮች ለማሳካት ያለውን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጡ የመግባቢያ ስምምነቶች መፈረሙን ጠቁመዋል። እነዚህ ስምምነቶች ኢትዮጵያ በፈጣን የለውጥ ጉዞ ያካበተችውን ልምድ ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ለማካፈል እንደ ወሳኝ መሠረት ያገለግላሉ ብለዋል። በተጨማሪም ስምምነቶቹ ከአጋሮች የተለያዩ ዕይታዎችን በመቅሰም ለአኅጉሩ ዕድገት ዘላቂና አፍሪካዊ መፍትሄዎችን በጋራ ለማፍለቅ እንደ ወሳኝ መሰረት እንደሚያገለግሉ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ ከጋራ የጽናት ታሪክ የሚመነጭ ጥልቅና ዘመናትን የተሻገረ ግንኙነት አላቸው
Apr 14, 2026 1094
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 6/2018(ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ በቅኝ ግዛት ያልተገዙ፣ ለአኅጉሩ ነፃነትና አንድነት ድምፅ በመሆን ከጋራ የጽናት ታሪክ የሚመነጭ ጥልቅና ዘመናትን የተሻገረ ግንኙነት አላቸው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባጋሩት መልዕክት፤ ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት ኢትዮጵያ የገቡትን የላይቤሪያ ሪፐብሊክ ፕሬዝደንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ በብሔራዊ ቤተ-መንግሥት አቀባበል በማድረጌ ታላቅ ክብር ይሰማኛል ብለዋል። ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ በቅኝ ግዛት ያልተገዙ፣ ለአኅጉሩ ነፃነትና አንድነት ድምፅ በመሆን ከጋራ የጽናት ታሪክ የሚመነጭ ጥልቅና ዘመናትን የተሻገረ ግንኙነት እንዳላቸውም ገልጸዋል። ዛሬም እንደ ሁሌው ኢትዮጵያ ከሰፊ ገበታዋ ያላትን ታላቅ ዐቅምና ዘላቂ ወዳጅነት፣ አብረዋት ለሚጓዙ ሁሉ ለማካፈል ዝግጁ ናት ሲሉም አስፍረዋል። በዚህ መንፈስ ይህ ጉብኝት በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በማጠናከር፤ የጋራ ህልሞቻችንን በማይናወጥ መሠረት እና የመፈጸም ቁርጠኝነት ወሳኝ ምዕራፍ እንደሚሆን ጽኑ እምነት አለኝ ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመልዕክታቸው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከፖርቹጋል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፓውሎ ራንገል ጋር ተወያዩ
Apr 14, 2026 704
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከፖርቹጋል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ፓውሎ ራንገል ጋር ውይይት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ከፖርቹጋል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር የሁለትዮሽ ግንኙነት እና ቀጣይ ትብብሮችን ማጠናከር በሚቻልባቸው ቁልፍ መስኮች ዙሪያ መምከራቸውን ገልጸዋል።
ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ ወታደራዊ የኢንዱስትሪና የቴክኖሎጂ ትብብራቸውን ለማሳደግ ተስማሙ
Apr 14, 2026 827
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ ወታደራዊ የኢንዱስትሪና የቴክኖሎጂ ትብብራቸውን ለማሳደግ ተስማምተዋል። የመከላከያ ሚኒስትር አይሻ መሐመድ (ኢ/ር) ከላይቤሪያ ሪፐብሊክ መከላከያ ሚኒስትር ብርጋዲየር ጄኔራል ጄራልዲን ጃኔት ጆርጅ ጋር በአዲስ አበባ ተወያይተዋል። በዚሁ ወቅትም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ወታደራዊ ትብብር ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር በሚቻልባቸው ስትራቴጂካዊ ጉዳዮች ላይ መክረዋል። ሚኒስትር አይሻ (ኢ/ር) ኢትዮጵያ እና ላይቤሪያ የአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት መሆናቸውን አስታውሰው፤ ይህ የታሪክ ትስስር አሁን ላለው ወታደራዊ ትብብር ጠንካራ መሠረት የሚጥል መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በወታደራዊ ኢንዱስትሪና በዐቅም ግንባታ ዙሪያ በትብብር ለመሥራት ኢትዮጵያ ዝግጁ መሆኗንም አረጋግጠዋል፡፡ ብርጋዲየር ጄኔራል ጄራልዲን ጃኔት ጆርጅ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የሰላም ማስከበር ስምሪትን ጨምሮ በወታደራዊ ሳይንስ እና በዘመናዊ መከላከያ ግንባታ ያካበተችው ተሞክሮ ለላይቤሪያ ትልቅ ትምህርት የሚገኝበት መሆኑን ገልፀዋል። ላይቤሪያ ከኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ሰፊ ልምድ የመቅሰም ከፍተኛ ፍላጎት እንዳላትም አስታውቀዋል። በተለይም በስልጠና እና በቴክኒክ ዘርፎች የሁለቱን ሀገራት ወታደራዊ ትብብር ይበልጥ ለማሳደግ እንደሚሠሩ መናገራቸውን የመከላከያ ኦንላይን ሚዲያ ለኢዜአ የላከው መረጃ ያመላክታል።
በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምጽ መስጠት የሚያስችለንን የምርጫ ካርድ ውስደናል-የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪዎች
Apr 14, 2026 529
ወላይታ ሶዶ፤ ሚያዝያ 6 /2018(ኢዜአ)፡- በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምጽ መስጠት የሚያስችላቸውን የምርጫ ካርድ መውሰዳቸውን የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በመጪው ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ለሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ የመራጮች ምዝገባ እስከ ሚያዝያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም ድረስ ማራዘሙ ይታወሳል። ቦርዱ የምርጫ ሂደቱ አሳታፊና አካታች እንዲሆን ባሳወቀው ተጨማሪ የጊዜ ሰሌዳ መሠረት የመራጮች ምዝገባ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ቀጥሏል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪዎች የምዝገባው ጊዜ መራዘሙ፣ በተለያዩ ምክንያቶች ካርድ መውሰድ ላልቻሉ ዜጎች መልካም አጋጣሚ መፍጠሩን ተናግረዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ምልኪያስ ወልዴ "በምርጫው ድምፄን ለመስጠት ተመዝግቤ ካርድ ወስጃለሁ'' ይላሉ። ''የእኔ ድምፅ በተሻለ መልኩ ሀገርን የሚመራ ፓርቲ ወደ ሥልጣን እንዲመጣ ጉልህ ድርሻ እንዳለው ስለማምን ዴሞክራሲያዊ መብቴን ለመጠቀም ተዘጋጅቻለሁ" ብለዋል። ሌላዋ ወይዘሮ ተስፋነሽ ግርማ፣ ምርጫ የዜግነት ግዴታን ለመወጣትና ዴሞክራሲያዊ መብትን ለመጠቀም ሁነኛ መሣሪያ በመሆኑ፣ ካርድ ያልወሰዱ ዜጎች ጊዜው ሳይጠናቀቅ ካርድ ወስደው መዘጋጀት አለባቸው ብለዋል። አቶ መልካሙ ለማ በጊዜ ሰሌዳው መሠረት ካርድ ወስደው መዘጋጀታቸውን ተናግረው፣ የሀገሪቱን ልማት የሚያፈጥን የፖለቲካ ፓርቲ በመምረጥ ዴሞክራሲያዊ መብታቸውን ለመጠቀም መዘጋጀታቸውን አስረድተዋል። ነዋሪዎቹ፣ ምርጫው ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና አካታች ሆኖ እንዲጠናቀቅ የድርሻቸውን ለመወጣትና ለሚፈልጉት የፖለቲካ ፓርቲ ድምፅ ለመስጠት የምርጫ ካርዳቸውን በአግባቡ ይዘው የምርጫውን ቀን እየተጠባበቁ መሆናቸውን ጠቅሰዋል።
ለዘላቂ ሰላም፣ ልማትና ለዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ የተሻለ ይሰራል ያልነውን ፓርቲ ለመምረጥ ካርድ ወስደናል
Apr 14, 2026 524
ገንዳውኃ፣ ሚያዝያ 6/2018 (ኢዜአ)፡- ለዘላቂ ሰላም፣ ልማትና ለዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ የተሻለ ይሰራል ያሉትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ የሚያስችላቸውን ካርድ መውሰዳቸውን በምዕራብ ጎንደር ዞን የኮኪትና ገንዳ ውሀ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ ። ምርጫ ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን በመገንባት የህዝብን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ወሳኝ ሚና እንዳለው ይታወቃል። ለዚህም ህዝቡ በሂደቱ በንቃት በመሳተፍ መብትና ግዴታውን ሊወጣ እንደሚገባ ይታመናል ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎትም በዚሁ ጉዳይ ላይ በምዕራብ ጎንደር ዞን የኮኪትና ገንዳ ውሀ ከተማ ነዋሪዎችን ያነጋገረ ሲሆን ነዋሪዎቹም ለዘላቂ ሰላም፣ ልማትና ዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ የተሻለ ይሰራል ያሉትን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ካርድ መውስዳቸውን ተናግረዋል ። በዞኑ መተማ ወረዳ የኮኪት ከተማ ነዋሪ አቶ ሲሳይ ደሴ በምርጫው በንቃት በመሳተፍ ለዴሞክራሲያዊ ስርአት ግንባታ የበኩላቸውን ለመወጣት የምርጫ ካርድ መውሰዳቸውን ገልጸዋል። የሀገር ልማትና ሰላም ለማስቀጠል በምርጫው በንቃት መሳተፍና የድምፅ መስጫ ካርድን መያዝ ወሳኝ መሆኑን ገልፀው በተለያዩ አማራጮች የሚተላለፈውን የምርጫ ቅስቀሳ እየተከታተሉ መሆናቸውን ጠቁመዋል። ሌላው በኮኪት ምርጫ ጣቢያ የመራጭነት ካርድ የወሰዱት አቶ ምስጋናው አለኸኝ በበኩላቸው፤ የአካባቢውን ሀብትና ፀጋ ተጠቅሞ የህዝቡን ተጠቃሚነት ሊያረጋግጥ የሚችል ፓርቲን ለመምረጥ መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። እንዲሁም የአካባቢውን የሰላም ሁኔታ በዘላቂነት የሚያሻሽል የህዝቡን መሰረታዊ ጥያቄዎች መመለስ የሚችል ፓርቲን እንደሚመርጡ አረጋግጠዋል። በቅድመ ምርጫ ያለው ሰላማዊ ሂደት በምርጫ እለትና ከምርጫ በኋላ አስተማማኝ ሆኖ እንዲዘልቅ የድርሻቸውን እንደሚወጡም አመላክተዋል። ምርጫው ሰላማዊና ፍትሀዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የህዝቡ ድርሻ ከፍተኛ በመሆኑ ለተግባራዊነቱ የበኩላቸውን እየተወጡ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ በዞኑ የገንዳውሃ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ሞሚና ዑመር ናቸው። ሰላምን ለማስፈንና የህዝብን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎችን የሚፈታ የፖለቲካ ፓርቲን ለመምረጥ ቀድመው ካርድ መያዛቸውን ተናግረዋል። "ምርጫ ዘላቂ ሰላምን ለማምጣት መፍትሄ መሆኑን አምነን ካርዳችንን በእጃችን ይዘናል" ያሉት ደግሞ ሌላው የገንዳ ውሀ ከተማ ነዋሪ አቶ ገብሬ አዱኛ ናቸው። በምርጫው የሚኖራቸው ተሳትፎ ለዴሞክራሲ ግንባታ ወሳኝ መሆኑን በመገንዘብ በምርጫው እለት ይመራኛል ለሚሉት የፖለቲካ ፓርቲ ድምጻቸውን በመስጠት ኃላፊነታቸውን እንደሚወጡ አመላክተዋል። በምዕራብ ጎንደር ዞን የምርጫ ጣቢያ አስተባባሪዎች በበኩላቸው፣ የካርድ መስጠት ሂደቱ በሰላማዊ መንገድ እየተከናወነ መሆኑንና ህብረተሰቡም በንቃት እየተሳተፈ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። ጠቅላላ ምርጫው ኢትዮጵያ የጀመረችውን የዴሞክራሲ ጉዞ ለማጠናከርና የተረጋጋ የፖለቲካ ስርዓት ለመፍጠር ትልቅ ሚና እንደሚኖረው ይጠበቃል።
የላይቤሪያው ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ ለስራ ጉብኝት ኢትዮጵያ ገቡ
Apr 13, 2026 1765
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 5/2018 (ኢዜአ)፦ የላይቤሪያው ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ ለስራ ጉብኝት ማምሻውን አዲስ አበባ ገብተዋል። የላይቤሪያ ፕሬዝዳንት ጆሴፍ ንዩማ ቦአካይ የነገ ብሩህ ተስፋ እየተሰራባት ወደ ምትገኘው ምድረቀደምት ኢትዮጵያ እንኳን በሰላም መጡ ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የእንኳን ደህና መጡ መልዕክት አስተላልፈዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም በፕሬዝዳንቱ ቆይታ እጅግ ፍሬያማ ውይይት እንደሚኖራቸው ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።
ወጣቶችን በልማት ተጠቃሚ የሚያደርግ የፖሊሲ አማራጭ ያለውን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅተናል
Apr 13, 2026 1425
ሰመራ፤ ሚያዚያ 5/2018 (ኢዜአ)፦ ወጣቶችን በልማት ተጠቃሚ የሚያደርግ የፖሊሲ አማራጭ ያለውን የፖለቲካ ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅተናል ሲሉ የሰመራ ሎጊያ ከተማ ወጣቶች ተናገሩ። በኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ከየካቲት 28 ቀን 2018 ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው የመራጮች ምዝገባ እስከ ሚያዝያ 14 ቀን 2018 ዓ.ም መራዘሙ ይታወሳል። በዚሁ መሰረት በአፋር ክልል የሰመራ ሎጊያ ከተማ ወጣቶችም በምርጫው በንቃት በመሳተፍ ሀገራዊ ልማትን ለማስቀጠል እና የወጣቶችን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ የፖለቲካ አማራጭ ያለውን ፓርቲ ለመምረጥ ካርዳቸውን እየወሰዱ መሆኑን ነው የተናገሩት። ለመምረጥ የሚያስችላቸውን የምርጫ ካርድ የወሰዱ የከተማ አስተዳደሩ ወጣቶች ለኢዜአ እንደተናገሩት የምርጫ ካርድ መውሰድ አማራጭ ሀሳብ ያለውን ፓርቲ ለመምረጥ መሰረታዊ ጉዳይ ነው። ወጣት ሃጂ አብዱልለጢፍ፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ያላቸውን የፖሊሲ አማራጮች በሚዲያ በሚያደርጉት ክርክሮች በንቃት እየተከታተልኩ ነው ብሏል። ይህም በተለይም የወጣቶችን ጉዳይ ትኩረት አድርጎ የሚንቀሳቀሰውን ፓርቲ ለመምረጥ እንደሚያስችለው ጠቅሶ በምርጫው በንቃት ለመሳተፍም ጥሩ አጋጣሚ ፈጥሯል ብሏል። ሌላኛው የከተማው ወጣት አብዱ መሐመድ በምርጫው ለመሳተፍ የሚያስችለውን ካርድ መውሰዱን ተናግሯል። በካርዱም ይበጀኛል የሚለውንና የወጣቶችን ሁለንተናዊ ጥያቄዎች ለመመለስ የሚሰራን ፓርቲ ለመምረጥ ከወዲሁ መዘጋጀቱን ጠቁሟል ። የመራጮች ካርድ መውሰዱ ለዴሞክራሲያዊ ግንባታ የበኩሉን ለማበርከትና የዜግነት ግዴታውን ለመወጣት መሰረት በመሆኑ ይህንኑ ተግባራዊ ማድረጉንም አክሏል። የመራጭነት ካርድ መውሰዴ ይጠቅመኛል የምለውን ፓርቲ እንድመርጥ ያስችለኛል ያለው ደግሞ ወጣት የሱፍ መሐመድ ነው። በዚህም በምርጫው በንቃት በመሳተፍ ሀገራችን የጀመረችውን የልማት ጉዞ ከግብ ለማድረስና የወጣቶችን ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥ አማራጭ ፖሊሲ ያለውን ፓርቲን ለመምረጥ ተዘጋጅቻለሁ ሲል ተናግሯል።
የሐረር ከተማ ነዋሪዎች በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የመራጭነት ካርድ በመውሰድ ድምጻቸውን ለመስጠት ከወዲሁ ተዘጋጅተዋል
Apr 13, 2026 1152
ሐረር ፤ ሚያዚያ 5/2018 (ኢዜአ)፦በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ መሳተፍ የሚያስችላቸውን የመራጭነት ካርድ በመውሰድ ድምጻቸውን ለመስጠት ከወዲሁ መዘጋጀታቸውን የሐረር ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ባስቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ከየካቲት 28 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በየምርጫ ጣቢያዎች የመራጮች ምዝገባ እየተካሄደ ነው። በዚህም በሐረሪ ክልል የሚገኙ ነዋሪዎች በምርጫው ለመሳተፍ የሚያስችላቸውን የመራጭነት ካርድ በመውሰድ ላይ ናቸው። ከከተማው ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ፍሬህይወት አባይነህ ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት ከዚህ ቀደም በነበሩት አራት ሀገራዊ ምርጫዎች ላይ በመሳተፍ ይሆነኛል፣ ይበጃል የሚሉትን ፓርቲ መምረጣቸውን አስታውሰዋል። በመጪው ግንቦት በሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ ለመሳተፍ ከወዲሁ መዘጋጀታቸውን ጠቁመው፤ ለዚህም የመራጭነት ካርድ መውሰዳቸውን እና ድምጻቸውንም ለሀገር ልማትና እድገት ይሰራል ብለው ለሚያምኑት ፓርቲ እንደሚሰጡ ተናግረዋል። የከተማው ነዋሪ አቶ ሀብታሙ ሲፋ በበኩላቸው፤ የዜግነትና ህገ መንግስታዊ መብታቸውን በመጠቀም በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ለመሳተፍ የመራጭነት ካርድ እንደወሰዱ ተናግረዋል። በሚዲያ አማራጮች የሚተላለፈውን የፖለቲካ ፓርቲዎች ክርክር በአግባቡ በመከታተል ላይ እንደሚገኙ የተናገሩት አቶ ሀብታሙ፤ ይሆነኛል ለሚሉት ፓርቲ ድምጻቸውን ለመስጠት መዘጋጀታቸውን አስታውቀዋል። ምርጫው ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ መወጣት እንደሚገባም ተናግረዋል። በምርጫው የነቃ ተሳትፎ ለማድረግ የምንፈልገውን ፓርቲ ለመምረጥ የሚያስችል ካርድ ወስደናል ያሉት ደግሞ አጀባ አደም ናቸው። የሚበጀንን ፓርቲ ለመምረጥ ተዘጋጅተናል ያሉት አጀባ፤ ምርጫው ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊ እንዲሆን የበኩላቸውን ለመወጣት መዘጋጀታቸውንም ገልጸዋል።