ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
የቀይ ባህር ደህንነት እና የኢትዮጵያ ስትራቴጂካዊ ሚና
Aug 29, 2026 206
(በሙሴ መለሰ) በቀይ ባሕርና በኤደን ባሕረ-ሰላጤ ቀጣናዊ ሰላምና ፀጥታን ለማረጋገጥ በሚደረገው ዓለም አቀፍ ጥረት ውስጥ ኢትዮጵያ የሚኖራት ሚና ከፍተኛ ነው። የኢትዮጵያ አብዛኛው ወጪና ገቢ ሸቀጦች በባህር በር በኩል የሚተላለፉ በመሆኑ፣ በቀይ ባህር እና በኤደን ባህረ ሰላጤ የሚከሰቱ የፀጥታ መደፍረሶች ወይም የሎጂስቲክስ መስተጓጎሎች በቀጥታ በሀገሪቱ ብሔራዊ ኢኮኖሚ ላይ የራሱን ተጽዕኖ ማሳረፉ የማይቀር ነው። በሆርሙዝ ሰርጥ የተከሰተውን የጸጥታ ቸግር ተከትሎ የተለያዩ የዓለም ሃገራት የቀይባህር መስመር ከባቤል ሜንደብ እስከ ስዊዝ ቦይ ድረስ ያለው ደህንነት አሳስቧቸዋል። ይሄንን ስጋት ለማቃለልም ሆነ የተለያዩ ፍላጎቶቻቸውን መነሻ በማድረግ አንዳንድ ሃገራት በቀጣናው ካሉ የባህር ተጋሪ መንግስታት ጋር በመሆን የመሰረቷቸውን የጦር ሰፈሮች ቢያጠናክሩም አሁንም ቀጣናው በባህር ላይ ውንብድና፣ በህገ-ወጥ ንግድና የሰዎች ዝውውር ወንጀል ለስጋት የተጋለጠ ሆኖ ይገኛል። የአፍሪካ ቀንድ ሰላም ከቀይ ባህር ደህንነት ጋር በቀጥታ የተሳሰረ መሆኑን በጽኑ የምታምነው ኢትዮጵያ፣ ድንበር ተሻጋሪ የፀጥታ ስጋቶችን ለመከላከል በሚደረጉ የባለብዙ ወገን ውይይቶች ላይ በመሳተፍ የበኩሏን አስተዋጽኦ ታበረክታለች። በተለይም ህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን፣ የጦር መሳሪያ እና የአደንዛዥ ዕፅ ዝውውርን እንዲሁም የባህር ላይ ወንጀሎችን በጋራ ለመመከት የቀጣናው ሀገራት የተቀናጀ ምላሽ እንዲኖራቸው ድጋፍ ታደርጋለች። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ቀንድ አገራት ጋር ያላት መልክዐ ምድራዊ ትስስር እና የፀጥታ አጋርነት በቀይ ባህር ቀጣና መረጋጋት ውስጥ ወሳኝ ድርሻ አለው። በቀጣናው የሚከሰቱ ፖለቲካዊ አለመረጋጋቶች እና የጸጥታ ችግሮች በቀጥታ በሀገሪቱ ብሔራዊ ደህንነት ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ በመሆናቸው፣ ኢትዮጵያ ቀጣናዊ ሰላምን በዘላቂነት ለማረጋገጥ የትብብር አማራጭን ተከትላ እየሰራች ትገኛለች። የአፍሪካ ቀንድና የቀይባሕር ደኅንነት ሊለያዩ የማይችሉ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው። ኢትዮጵያ በሕዝብ ብዛቷ፣ በኢኮኖሚ እንቅስቃሴዋና በጂኦ-ፖለቲካዊ አቀማመጧ በቀጣናው ትልቅ ድርሻ ያላት በመሆኑ፣ በሚደረጉ የማሪታይምና የደኅንነት ውይይቶች ላይ የምታደርገው ንቁ ተሳትፎ ለቀጣናው ዘላቂ ሰላም መረጋገጥ አስፈላጊ ነው። ኢትዮጵያ በቀጣናው ያላትን ሰፊ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚዊ ተጽዕኖ በመጠቀም፣ ስትራቴጂያዊ የንግድ መስመሮችን ከስጋት ነፃ ለማድረግ በቁርጠኝነት እየሰራች መሆኑ በቅርቡ በናይሮቢ በተካሄደው ዓለም አቀፍ መድረክ በግልጽ ታይቷል። በኬንያ ናይሮቢ በተካሄደው አምስተኛው የቀይ ባህርና የኤደን ባህረ ሰላጤ የባህር ላይ ህግ ማስከበር ውይይት (Maritime Law Enforcement Dialogue) ላይ፣ የኢትዮጵያ ልዑካን ቡድን አገራዊና ቀጣናዊ ጥቅሞችን የሚያስጠብቅ ተሳትፎ አድርጓል። ይህም ኢትዮጵያ በቀጣናው ሰላምና የኢኮኖሚ ትስስር ላይ ያላትን ሚና እና ባለቤትነት አሳይቷል። ለኢትዮጵያ የባህር በር ደህንነት የህልውና ጉዳይ ነው። በውይይቱ ላይ የተሳተፉት የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለሥልጣን ተወካይ ካፒቴን ክብሩ መስፍን እንደገለጹት፣ የባሕር ላይ ሰላም መደፍረስ በቀጥታ የአገሪቱን ብሔራዊ ኢኮኖሚ ይነካል። አብዛኛው የሀገሪቱ ወጪና ገቢ ንግድ በባህር ላይ የሚካሄድ በመሆኑ፣ በቀይ ባህር ላይ የሚከሰቱ የባሕር ላይ ውንብድናዎችና ህገ-ወጥ እንቅስቃሴዎች የንግድ ፍሰቱን እንዳያስተጓጉሉ በቅንጅት መስራት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል። ካፒቴን ክብሩ አክለውም፣ የመርከቦች መድን ዋስትና መናርና የሸቀጦች መዘግየት የሀገሪቱን የንግድ ተወዳዳሪነት እንዳይፈታተኑ፣ ጠንካራና የተቀናጀ የባህር ላይ ቁጥጥር ሥርዓት መዘርጋት አማራጭ የሌለው ጉዳይ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። ይህን ዓለም አቀፋዊ ስጋትን ለመመከት ኢትዮጵያ የጋራ መፍትሔዎችን በማቅረብ ረገድ ግንባር ቀደም ናት። በተለይም ከጎረቤት አገራት ጋር በመቀናጀት "ብሔራዊ የማሪታይም መረጃ ማዕከል" (National Maritime Information Centre) ለመመስረት ያቀደችው ስትራቴጂ፣ ሀገሪቱ ለቀጣናው መረጋጋት ያላትን የረጅም ጊዜ ራዕይ የሚያሳይ ነው። መረጃን በጋራ መለዋወጥና የተቀናጀ የሕግ ማስከበር እርምጃ መውሰድ ለዚህ ስኬት ዋነኛው መሳሪያ እንደሆነ ኢትዮጵያ በጽኑ ታምናለች። በቀይ ባህርና በኤደን ባህረ-ሰላጤ የሚስተዋሉ እንደ ሕገ-ወጥ የሰዎችና የዕፅ ዝውውር እንዲሁም ሕገ-ወጥ አሳ ማጥመድ ያሉ ስጋቶች ድንበር ተሻጋሪ በመሆናቸው፣ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ቀጣናዊ ኃይሎች ተሳትፎ የዓለም አቀፍ ማህበረሰቡን ትኩረት ስቧል። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአደንዛዥ ዕፅና ወንጀል ጉዳዮች ቢሮ (UNODC) የቀጣናው አስተባባሪ ሞስታፋ ኤልባና እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ያላት የፖለቲካና የኢኮኖሚ አቅም ዓለም አቀፍ የንግድ መስመሮች አስተማማኝና የተረጋጉ እንዲሆኑ ትልቅ አስተዋጽኦ አለው። በቀይ ባህር ቀጣና ያላትን ስትራቴጂካዊ ጥቅም ለማስጠበቅና የጋራ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የምታደርገው ዲፕሎማሲያዊና ተግባራዊ እንቅስቃሴ ተጠናክሮ ቀጥሏል። የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአደንዛዥ ዕፅና ወንጀል ጉዳዮች ቢሮ (UNODC)፣ ኢንተርፖል እና ዓለም አቀፉ የፍልሰት ድርጅት (IOM) የመሳሰሉ ዓለም አቀፍ ተቋማት እንዲሁም ከጎረቤት ሀገራት ጋር በቅርበት በመሥራት ኢትዮጵያ በቀጣናው ሰላምና ጸጥታ ላይ ያላትን የመሪነት ሚና በታሪካዊ ኃላፊነትና በሕግ አግባብ እያስጠበቀች ትገኛለች። ኢትዮጵያ የባህር ኃሃይልን ጨምሮ በጥብቅ ዲሲፕሊኑ እና በመፈጸም አቅሙ የሚታወቅ ጠንካራ የመከላከያ ሰራዊት ገንብታለች። ይሄ ሰራዊት በተለያየ ጊዜ ችግር ላጋጠማቸው ሃገራት ባሳየው የሰላም ማስከበር ሚናው በውጤታማነቱ የተመሰከረለትም ነው። የቀጣናውን ደህንነት ለመጠበቅ የሚያስችል ጠንካራ ሃይል አስፈላጊ ስለሆነም በቅርብም በሩቅም ያሉ ሃገራት የኢትዮጵያን የባህር ላይ ህልውና በበጎ ይመለከቱታል። ለዚህም በቅርቡ በአንድ የሃገር ውስጥ ሚዲያ በሰጡት ቃለ-መጠይቅ የባብኤል ሜንደብን እና የቀጣናውን ሰላም ለማስጠበቅ ሃገራቸው በቂ አቅም ስለሌላት የሌሎች እገዛ አስፈላጊ መሆኑን የተናገሩት የጅቡቲ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ፋይናስ ሚኒስትር ኢሊያስ ሙሳ ዳዋሌህ ገለጻ አንዱ ማሳያ ነው። እነዚህ ሁሉ ጉዳዮች አመላካች የሚሆኑት ያለ አግባብ ከባህሩ የተገፋችውና መብቷን የምትጠይቀው ኢትዮጵያ ያላት ዘርፈ ብዙ ዓቅም ለቀጣናውም ለራሷም ሰላምና ደህንነት መረጋገጥ ወሳኝ ሚና ያላት መሆኑን ነው።
የኢትዮጵያን የባሕር በር ጥያቄ ጎረቤት ሀገራት በአግባቡ ሊረዱት የሚገባ መሠረታዊ ጉዳይ ነው - የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፑዋንግኬትኬው
Aug 29, 2026 143
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፤ የኢትዮጵያን የባሕር በር ጥያቄ ጎረቤት ሀገራት በአግባቡ ሊረዱት የሚገባ መሠረታዊ ጉዳይ መሆኑን የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፑዋንግኬትኬው ገለጹ። ኢትዮጵያ ካላት የሕዝብ ቁጥርና ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት አንጻር የባሕር በር የማግኘት ጉዳይን የህልውና አጀንዳ አድርጋ እየሰራች ትገኛለች። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የቀጣናው ግዙፍ ሀገር የሆነችው ኢትዮጵያ የጂኦግራፊ እስረኛ ሆና መቀጠል እንደማትችል በተደጋጋሚ መግለጻቸው ይታወቃል። ኢትዮጵያ ይህንን ጥያቄዋን በንግድና ሰጥቶ መቀበል መርህ ለማሳካት በቀጣይነት እንደምትሰራም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መናገራቸው አይዘነጋም። በኢትዮጵያ ይፋዊ ጉብኝት ያደረጉት የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፑዋንግኬትኬው ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ የባሕር ወደቦች ለአንድ ሀገር ንግድና ኢንቨስትመንት እጅግ ወሳኝ መሆናቸውን አመልክተዋል። በመሆኑም ኢትዮጵያ የባህር በር ለማግኘት የምታደርገውን ጥረት ጎረቤት ሀገራት በአግባቡ ሊረዱት የሚገባ መሠረታዊ ጉዳይ መሆኑን ተናግረዋል። የባሕር በር የማግኘት ሂደቱ ከጎረቤት ሀገራት ጋር የጋራ ጥቅምና ዕድገትን መሰረት ባደረገ መልኩ ሊከናወን እንደሚገባም አመልክተዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ በማደግ ላይ ባሉ ሀገራት መካከል ሊኖር ከሚገባው የትብብር ማዕቀፍ ጋር የሚተሳሰር መሆኑንም ነው ያነሱት። በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በዓለም አቀፍ የዲፕሎማሲ መድረኮች ድምፃቸውና ፍላጎታቸው ተሰሚነት እንዲያገኝ በጋራና በትብብር መስራት እንዳለባቸውም ነው የተናገሩት። በተጨማሪም የደቡብ ንፍቀ ክበብ ሀገራት በዓለም አቀፉ ሥርዓት ውስጥ ጥቅሞቻቸውን ለማስጠበቅ ከመቼውም ጊዜ በላይ በትብብር መስራት እንዳለባቸው ጠቅሰው፤ አፍሪካ ለዚህ ትብብር ዋነኛዋ ድምጽ ሆና እየወጣች ስለመሆኑም አብራርተዋል። ኢትዮጵያ የህብረቱ መቀመጫ እንደመሆኗ መጠን አፍሪካን ከኢስያ አህጉር ጋር በማስተሳሰር ረገድ መግቢያ በር ሆና እያገለገለች እንደምትገኝም የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፑዋንግኬትኬው ተናግረዋል። ትብብርን እና በሕግ ላይ የተመሠረተውን ዓለም አቀፍ ሥርዓት ለማስጠበቅ ተመሳሳይ አመለካከት ባላቸው ሀገራት መካከል የበለጠ ወዳጅነት እና አንድነት እንዲኖርም ጥሪ አቅርበዋል።
ለውጥ እና ነውጥ፤ የአትክልተኛው ማስታወሻ የተሰኘ አዲስ መጽሐፍ ነገ ይመረቃል
Aug 29, 2026 273
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ) ፦ ፖለቲከኛ ግርማ ሰይፉ በባለፉት ስምንት ዓመታት በኢትዮጵያ የታዩትን የለውጥ ሒደቶችና የፖለቲካ ውጣ ውረዶችን የሚተነትን "ለውጥ እና ነውጥ፤ የአትክልተኛው ማስታወሻ" የተሰኘ አዲስ መጽሐፋቸውን ነገ ያስመርቃሉ። ነገ ነሐሴ 24 ቀን 2018 ዓ.ም በአድዋ ድል መታሰቢያ 9:00 ላይ የሚመረቀውን መጽሐፍ ምክንያት በማድረግ አቶ ግርማ ሰይፉ ለኢዜአ እንዳሉት፤ መጽሐፉ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ባህል ከጸብና ከጠመንጃ መራቅ እንዳለበት ለማስገንዘብ እና የተዛቡ ትርክቶችን ለማስተካከል አዎንታዊ ሚና ይኖረዋል። መጽሐፉ የተሳካና የተሟላ የሀገረ መንግሥት ግንባታን ዕውን ለማድረግ ጠቃሚ ምክረ-ሀሳቦችን ያቀረበ መሆኑን ጠቁመዋል። ልዩነቶችና አለመግባባቶች በምክክር ብቻ መፈታት እንዳለባቸው በመግለጽ፣ የብሔራዊ ምክክርን አስፈላጊነት በአጽንኦት አንስተዋል፡፡ መጽሐፉ ወጣቶች በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የዳር ተመልካች ሳይሆኑ መሪ ተዋናይ እንዲሆኑ እንደሚያስገነዝብ ገልጸው፤ ከመገፋፋት ይልቅ ሁሉም ወገን በትብብር ለመሥራት ፈቃደኛ መሆን አለበት ብለዋል። ኢትዮጵያውያን በጋራና በትብብር ሲቆሙ ብቻ ፈተናዎችን መሸጋገር፣ እንዲሁም ድህነትንና ኋላቀርነትን ማሸነፍ እንደሚችሉ መጽሐፉ ማብራራቱን ተናግረዋል። በነገው ዕለት በሚካሄደው የመጽሐፉ የምርቃት ሥነ-ሥርዓት ላይ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችን ጨምሮ የተለያዩ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ይገኛሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጸዋል። መጽሐፉ በስድስት ምዕራፎች የተከፋፈለና 270 ገጾች ያሉት መሆኑን ገልጸዋል። በነገው ዕለት በይፋ ከተመረቀ በኋላ በሁሉም መጽሃፍት መድብሮች ለገበያ እንደሚቀርብ ተናግረዋል።
ለተሻለ ነገ መሰረት የጣለው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ
Aug 29, 2026 229
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ሀገራዊ መግባባትን በማጠናከር የኢትዮጵያን አንድነትና እድገት ለማረጋገጥ ወሳኝ ምዕራፍ መሆኑን አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ። ከሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ለአርባ ስድስት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የኢትዮጵያ ዋናው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ በስኬት ተጠናቋል። በጉባኤው ኢትዮጵያውያን ለዘመናት የዘለቁ የአለመግባባት ስብራቶችን በሐሳብ የበላይነትና በጥበብ መፍትሔ መስጠት እንደሚችሉ በተግባር አሳይተዋል፡፡ ኢዜአ ያነጋገራቸው የመዲናዋ ነዋሪዎች እንደገለጹት፤ ምክክሩ ኢትዮጵያ ወደ አንድነትና የተሻለ ልማትና እድገት የምትሸጋገርበት ትልቅ ድል ነው። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ሀምሳ አለቃ አብዱ ሁሴን እንደገለጹት፤ ምክክሩ ሁሉንም የማህበረሰብ ክፍሎችን ያካተተ፤ ለሀገር የሚበጁ ጉዳዮች ላይ የተመካከሩበት ስኬታማ ሁነት ነው። ምክክሩ ለዘመናት የዘለቁ አለመግባባቶችን ለመፍታት ችግሮችን በምክክር ወደ ጠረጴዛ ዙሪያ ለማምጣት ያስቻለ መሆኑን ገልጸው፤ የአንድነት የአብሮነት እሴቶች እንዲጎለብቱ ያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። ሌላዋ አስተያየት ሰጪ ወይዘሮ ሃሊማ መሃመድ በበኩላቸው፤የሀሳብ ልዩነትን በኃይል ለመፍታት መመኮር ጊዜው ያለፈበት አካሄድ መሆኑን ጠቁመዋል። ምክክሩ ችግሮችን በሰለጠነ መንገድ ለመፍታት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ጠቅሰው፤በምክክር የምትገነባ ሀገር አሸናፊ ናት አሁን ኢትዮጵያ የአሸናፊነት ጉዞዋን ጀምራለች ብለዋል። ምክክሩ ለትውልድ የሚበጅና ለሀገር አንድነት መሰረት የተጣለበት ከመሆኑም በላይ ለሌሎች ሀገራትም ምሳሌ የሚሆን ነው ያሉት ደግሞ አቶ አበበ ኮምቤ ናቸው። ወይዘሮ ዘሪቱ አስቤ በበኩላቸው፤ቀደም ሲል በሀገሪቱ ችግሮችን ለመፍታት በጠረጴዛ ዙሪያ የመመካከር ልምድ እንዳልነበረ አንስተዋል። ምክክሩ በችግሮች ላይ በመመካከርና በመፍታት ኢትዮጵያን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሻገር ትልቅ ፋይዳ አለው ብለዋል።
ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመገንባትና ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶችን ለማፋጠን የሚከናወኑ ተግባራት የሚበረታቱ ናቸው
Aug 29, 2026 228
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 23/2018 (ኢዜአ)፦ ጠንካራ ኢትዮጵያን ለመገንባትና ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶችን ለማፋጠን የሚከናወኑ ተግባራት የሚበረታቱ መሆናቸውን ኢዜአ ያነጋገራቸው የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ገለጹ። ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል ወጣት ፉአድ መሀመድ ጠንካራ ሀገረ መንግሥት ለመገንባት ዜጎች እርስ በእርስ በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት የሚፈጥሩበት አውድ ማመቻቸት አስፈላጊ መሆኑን ገልጿል። ይህንንም ኢትዮጵያ ባካሄደችው ሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ማሳካት መቻሏን ተናግሯል። የሀገሪቱን ሁለንተናዊ እድገት ለማፋጠን በፖለቲካው ዘርፍ ከሚሰሩ ተግባራት ባለፈ ግዙፍ ሜጋ ፕሮጀክቶች ግንባታቸው በፍጥነት ተጠናቆ የተመረቁበት እና አዳዲስ ደግሞ የተጀመሩበት ሁኔታ መኖራቸው ለሀገር እድገት ሚናቸው የጎላ መሆኑን አንስቷል። ለአብነት በሀገር እና በህዝብ ጥረት ተገንብቶ አገልግሎት መስጠት የጀመረውን የሕዳሴ ግድብ በማንሳት ፕሮጀክቱ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት እንዲሻሻል እና ኢንዱስትሪዎች እንዲስፋፉ ያደረገ መሆኑን የሚያኮራ ተግባር ነው ሲል ገልጿል። ትልልቅ የልማት ፕሮጀክቶችን ለመገንባት የሚደረጉ ጥረቶች የወጣቶችን ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ እንደሆነም ተናግሯል። ሌላኛዋ አስተያየት ሰጪ ወጣት ራህመት ዲኖ በበኩሏ፤ ኢትዮጵያ ሰባተኛውን ጠቅላላ ምርጫ በተሳካ ሁኔታ በማካሄድ ለጠንካራ ሀገረ መንግሥት ግንባታ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር ማረጋገጧን ገልጻለች። እኛ ዜጎችም ከመንግሥት ጋር በጋራ የተጀመሩ የልማት ሥራዎች በላቀ ደረጃ እንዲቀጥሉ ተሳትፏችንን ልናጠናክር ይገባል ብላለች። የሀገርን ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ፣ ልማትን ለማፋጠን እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት የሚበረታቱ መሆናቸውን የገለጸው ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ወጣት ዘሪሁን ፍቃዱ ነው። ሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ በሆነና ህዝቦችን በነቂስ ባሳተፈ መንገድ መከናወኑ የዴሞክራሲ አካሄዳችን እየዳበረ መሆኑን ማሳያ ነው ብሏል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ዮናስ ደስታ በበኩሉ፤ መንግሥት ፕሮጀክቶችን ጀምሮ በማጠናቀቅ ዜጎችን ተጠቃሚ ለማድረግ እየወሰደ ያለው ቁርጠኛ እርምጃ የሚደነቅ ነው ብሏል። ለጠንካራ ሀገረ መንግስት ግንባታ መሰረት እየተጣለ መሆኑ የኢትዮጵያ የወደፊት ዕጣ ፋንታ ብርሀኑ የሚያደርግ ተጠቃሽ እርምጃ መሆኑንም ተናግሯል። በቀጣይም የኢትዮጵያን ብልጽግና እውን ለማድረግ ሕዝቡ በልማቱ ንቁ ተሳታፊ እንዲሆን በመንግሥት የሚደረጉ ጥረቶች ሊቀጥሉ እንደሚገባ አመልክቷል።
የምክክር መድረኩ የቆዩ ችግሮችን በውይይት በመፍታት ሀገርን የማሻገር ፅኑ ፍላጎት የታየበት ነው
Aug 28, 2026 325
ጂንካ፤ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ) ፡-ሀገራዊ የምክክር መድረኩ የቆዩ ችግሮችን በውይይት በመፍታት ሀገርን የማሻገር ፅኑ ፍላጎት የታየበት መሆኑን ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የጂንካ ከተማ ነዋሪዎች ገለፁ። ሀገራዊ የምክክር ጉባኤው የተሻለች ሀገርን የመገንባት አዲስ ተስፋን የፈነጠቀና ለችግሮች በውይይት መፍትሔን በመሻት ሀገርን የማሻገር አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ የተከፈተበት ታሪካዊ አጋጣሚ ነው። በመድረኩ ላይ የተደመጡት የጋራ እይታዎች፣ የሰጡት ገንቢ አስተያየቶችና የታየው የነቃ ተሳትፎ ህዝቡ ያለፉ አለመግባባቶችን በመሻገር ወደ ተሻለ የታሪክ ምዕራፍ ለመሸጋገር ያለውን ፅኑ ፍላጎትና የጋራ ቁርጠኝነት ግልጽ አድርጎ ያሳየ ነበር። ኢዜአ ያነጋገራቸው የጂንካ ከተማ ነዋሪዎችም፤ የምክክር መድረኩ የቆዩ ችግሮችን በውይይት በመፍታት ሀገርን የማሻገር ፅኑ ፍላጎት የታየበት ነው ብለዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ጋሻው ገላው፤ ምክክር ለሀገር ብቻ ሳይሆን በግል ህይወትም ችግሮችን ቀርፎ የተሻለ ህይወት ለመምራት አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። ሀገራዊ የምክክር መድረኩ አለመግባባቶችን በውይይትና በምክክር የመፍታት መሠረት መጣሉን የጠቆሙት አቶ ጋሻው፤ ተነጋግሮ የመግባባት ባህል እንዲጎለብት ማስቻሉንም ገልጸዋል። መሰረቷ የፀናች ህብረ-ብሔራዊት ሀገርን ለመገንባት የእያንዳንዱ ዜጋ ተሳትፎ ወሳኝ እንደሆነ ያነሱት ደግሞ አቶ ቅዱስ መንገሻ ናቸው። በሀገራዊ የምክክር መድረኩ የተነሱ ሀሳቦች ብዙሃኑን ያማከሉ፣ አካታችና ሀገር የሚያሻግሩ በመሆናቸው፤ ለተፈጻሚነታቸው ሁሉም ዜጋ የበኩሉን ሚና ሊወጣ እንደሚገባ ገልጸዋል። ሀገርን ማሻገር ከተፈለገ ከግል ፍላጎት ይልቅ የሀገርን ፍላጎትና ብሔራዊ ጥቅም ማስቀደም እንደሚገባም አብራርተዋል። "ችግሮቻችንን በውይይት የመፍታት ዕድል በማጣታችን በጥቃቅን ጉዳዮች አለመግባባት ውስጥ የምንገባበት ጊዜ አብቅቶ አዲስ የዲሞክራሲ ምህዳር ተፈጥሯል" ያሉት ደግሞ ሌላው የጂንካ ከተማ ነዋሪ አቶ እሸቱ ፈይሳ ናቸው። የምክክር መድረኩ የሀሳብ የበላይነት የታየበትና ሀገርን ወደ ለውጥ ምዕራፍ ለማሻገር በህዝቡ ውስጥ ያለውን ጉጉትና ፅኑ ፍላጎት ያየንበት ነው ብለዋል። በምክክር መድረኩ የተነሱ ሀሳቦች ተፈጻሚ ሆነው የታለመው ሀገራዊ መግባባትና ዘላቂ ሰላም እንዲመጣ ሁላችንም ኃላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል ሲሉም አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ ከታይላንድ ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊና ፖለቲካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ የኢኮኖሚ ትብብር ለማሳደግ ትሰራለች- የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር)
Aug 28, 2026 383
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ) ፦ ኢትዮጵያ ከታይላንድ ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊና ፖለቲካዊ ግንኙነት ወደ ላቀ የኢኮኖሚ ትብብር ለማሳደግ እንደምትሰራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ከየታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፑዋንግኬትኬው ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርገዋል። ሚኒስትሮቹ የሁለቱን ሀገራት ፖለቲካዊ፣ ዲፕሎማሲና የኢኮኖሚ ትብብር ለማሳደግ የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) በዚህ ወቅት በኢትዮጵያና ታይላንድ መካከል ያለውን የዲፕሎማሲና ፖለቲካ ግንኙነት ወደ ኢኮኖሚያዊ ትብብር ማሳደግ የሚያስችል ገንቢ ውይይት አድርገናል ብለዋል። ይህም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ማጠናከር እንደሚያስችልም ገልጸዋል። የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉዋንግኬትክየው በበኩላቸው፤ ታይላንድ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትና ትብብር ማጠናከር ትፈልጋለች ብለዋል። የተፈረመው የመግባቢያ ስምምነት የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብርን በማጠናከር ኢትዮጵያ በግብርናው ዘርፍ ያላት እምቅ አቅም ላይ እሴት መጨመር የሚያስችል ልምዳችንን እናካፍላለን ብለዋል። በተጨማሪም ሁለቱ ሀገራት የደቡብ-ደቡብ ትብብርን ለማጠናከር በጋራ እንደሚሰሩም ተናግረዋል። ታይላንድ በቅርቡ ኤምባሲዋን በአዲስ አበባ በመክፈት ትብብሯን ወደ ላቀ ደረጃ ታሸጋግራለች ብለዋል። የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉዋንግኬትክየው ለይፋዊ የስራ ጉብኝት እና ታሪካዊውን “የታይላንድ-አፍሪካ ኢኒሼቲቭ” በይፋ ለማስጀመር አዲስ አበባ የገቡት ዛሬ ማለዳ ነበር።
የኢትዮጵያውያን የወል እውነት- ሀገራዊ ምክክር
Aug 28, 2026 413
በሙሴ መለስ ኢትዮጵያ የበርካታ ብሔር ብሔረሰቦች እና ህዝቦች የጋራ መኖሪያ እና የብዝሃነት ውበት ደምቆ የሚታይባት ሀገር ናት ። ዛሬ ላይ ለመድረስም በርካታ ውጣ ውረዶችን፣ እና የታሪክ ምዕራፎችን ተሻግራለች። በነዚህ ምዕራፎች ውስጥም በአብሮነትና በጋራ ሃገራዊ እሳቤ ከተገነቡት የጋራ ማንነቶች ባልተናነሰ መልኩ ያጋጠሙ የታሪክ ስብራቶች የልዩነት እና ያለመግባባት መንስኤ የሚሆኑበትን አጋጣሚም አስተናግዳለች። ልዩነቶችን በጉልበት ወይም በኃይል ሳይሆን፣ በጠረጴዛ ዙሪያ በመነጋገር እና ከነጣይ ትርክት ይልቅ ወደ ሃገራዊ መግባባትና የጋራ ጉዳዮች ላይ በማተኮር ብሔራዊ መግባባትን ለማምጣትም ሃገራዊ ምክክሩ የራሱን ቁልፍ ሚና በመወጣት በሃገራችን ታሪክ አዲስ ምዕራፍ የከፈተ መሆኑ ይታወቃል። ከአራት ዓመታት በፊት የተቋቋመው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን፣ ከቀበሌ ጀምሮ እስከ ሀገር አቀፍ ደረጃ ሰፊ ህዝባዊ ውይይቶችን በማድረግ የህብረተሰቡን አጀንዳዎች በባለቤትነት የማሰባሰብ ሂደቱን በስኬት አከናውኗል። የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሲቪክ ማህበራት፣ ምሁራን፣ ዳያስፖራዎችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች በአንድ መድረክ የተሳተፉበት የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ለ46 ቀናት ተካሄዶ በስኬት መጠናቀቁ ተበስሯል። ይህ ጉባኤ ዜጎች ሃሳባቸውን በነፃነት የገለጹበት፣ የጋራ መግባባት ላይ የደረሱበት በሀገሪቱ የፖለቲካ ታሪክ ውስጥም የጠመንጃ የበላይነትን በማስቀረት፣ የሀሳብ የበላይነትና የሰላማዊ የውይይት ባህልን ለማስፈን ምቹ ምህዳር የፈጠረ አካታች አካሄድ ነው። ከጉባኤው የተገኙ ምክረ-ሐሳቦችና የተገኙት ልምዶች ወደ ተግባር እየተሸጋገሩ፣ በየደረጃው በሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች መካከል ውይይቱ ተጠናክሮ የሚቀጥልበትን አዲስ ምዕራፍ የሚከፍትም ነው። የጋራ ትርክት ህዝቦች በታሪካቸው፣ በአሁኑ ሁኔታቸው እና በወደፊት ዕጣ ፈንታቸው ላይ ያላቸው የጋራ መረዳትና ስምምነት ሲሆን ይህም አብሮነትን ለማጎልበት ጠንካራ መሰረት ይጥላል። ለዘመናት በጦርነት፣ በኃይልና በፖለቲካ ሽኩቻ ሲንከባለሉ የቆዩ የትርክት ስብራቶችም ከጠመንጃ ይልቅ በሰላማዊ መንገድ በጠረጴዛ ዙሪያ ክርክር ለመፍታት ስለመቻሉም ትልቅ ማሳያ ነው። በምክክሩ ላይ በመላው ሃገሪቱ አሉን የሚሏቸውን ጥያቄዎችና ቅሬታዎች በኃይል በጦር መሳሪያ ለመፍታት ነፍጥ አንግበው ሲታገሉ የነበሩ አካላት ሁሉ እንዲሳተፉ መደረጉም የሒደቱን ስኬታማነት ለዓለም ማህበረሰብ ያሳየ ነው። ከተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች፣የፖለቲካ አመለካከቶችና የኅብረተሰብ ክፍሎች የተወጣጡ አራት ሺህ ተመካካሪዎች የየራሳቸውን የተናጠል ፍላጎት ብቻ ከማንጸባረቅ ተቆጥበው በተለዩ ስምንቱ አበይት አጀንዳዎች ላይ በጋራ መስማማታቸውም የወል ትርክት ግንባታን የውጤታማነት ጉዞ ስኬት በተግባር የገለጠ ነው። ይህ ለግል ወይም ለቡድን ጥቅም ሳይሆን ለሀገር ህልውና እና ለጋራ ዕድገት ቅድሚያ የመስጠት ትልቅ የፖለቲካ ብስለትም ነው። ይህ ሂደት እያንዳንዱ ዜጋ በሀገሩ ላይ ሙሉ ባለቤትነትና ደህንነት እንዲሰማው የሚያደርግ ሲሆን የጋራ አገርና የጋራ ዕድል አለን የሚለውን እሳቤ በማጉላትም የወል ትርክትን በጽኑ መሠረት ላይ ይገነባል። ምክክሩ በጥቂት የፖለቲካ ልሂቃን (Elites) መካከል ብቻ የተደረገ ውይይት ሳይሆን እስከ ወረዳ ድረስ ያሉትን የታችኛውን የህብረተሰብ ክፍሎች፣ አርሶ አደሮችን፣ አርብቶ አደሮችንና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ያሳተፈ መሆኑም ትልቅ ትርጉም አለው። ከሕዝብ ቀጥተኛ ተሳትፎ የፈለቁት ምክረ ሀሳቦች ለሀገራዊ ትርክት መጠንከር ወሳኝ ሚና ከመጫወት ባለፈ ሂደቱ በህዝቡ ዘንድ ሙሉ ተቀባይነት ያለው እንዲሆን ያደርገዋል። ምክክሩ ያረጋገጠው ትልቁ እውነት የኢትዮጵያውያን ዕጣ ፈንታ የተሳሰረ መሆኑንና የወል ትርክት ግንባታ የሀገር ህልውና ዋስትናነቱን ነው። ልዩነቶችን ውበት፣ ውይይትን ደግሞ መሳሪያ በማድረግ የተጀመረው ይህ ጉዞ ኢትዮጵያ በቀደመ ታሪኳ የገጠሟትን የታሪክ ስብራቶች በመጠገን ወደ ዘላቂ ብልጽግና፣ ዲሞክራሲና እውነተኛ አንድነት እንድትሸጋገር ያስችላታል።
ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ከታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር ተወያዩ
Aug 28, 2026 312
አዲስ አበባ ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ) ፦የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ከታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉዋንግኬትክየው ጋር በብሔራዊ ቤተመንግሥት ተወያይተዋል። የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉዋንግኬትክየው ለይፋዊ የስራ ጉብኝት እና ታሪካዊውን “የታይላንድ-አፍሪካ ኢኒሼቲቭ” በይፋ ለማስጀመር ዛሬ አዲስ አበባ መግባታቸው ይታወቃል። ዛሬ ከሰዓት ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ከምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጋር በብሔራዊ ቤተመንግሥት ተወያይተዋል። በኢትዮጵያ እና በታይላንድ መካከል እያደገ የመጣውን የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ ወደ ላቀ ደረጃ ማሻገር በሚያስችሉ ጉዳዮች ዙሪያ መምከራቸውም ተገልጿል።
ሀገራዊ ምክክሩ ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለች ሀገር ለማስረከብ ትልቅ አቅምን የፈጠረ ነው- የጽህፈት ቤቱ አባላት
Aug 28, 2026 239
ደሴ፤ ነሐሴ 22/2018(ኢዜአ)፡- ሀገራዊ ምክክሩ ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለች ሀገር ለማስረከብ ትልቅ አቅምን የፈጠረ ነው ሲሉ የደቡብ ወሎ ዞን ጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ጽሕፈት ቤት አባላት ገለጹ። በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን፣ ሀገራዊ መግባባትን ለማጠናከር እና መሠረታዊ በሚባሉ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ አቋም ለመያዝ ሲካሄድ የቆየው ሀገራዊ የምክክር ሂደት በስኬት ተጠናቋል። በሂደቱ ከሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች የተወከሉ አካላት፣ የተለያዩ የፖለቲካ ኃይሎች እና ባለድርሻ አካላት በመሳተፍ ልዩነቶችን በውይይት በመፍታት ረገድ አዲስ ምዕራፍ የተከፈተ ሆኖ ተገኝቷል። በዚህም የተገኙ ውጤቶችና የቀረቡ የፖሊሲ አስተያየቶች ወደፊት ለሚከናወኑ ሀገራዊ የሪፎርም ሥራዎች እና ለዘላቂ ውሳኔዎች መሠረት የሚሆኑ ናቸው። የጽሕፈት ቤቱ ፀሐፊ ተተኪ አርበኛ አየለ ወልደ ጊዮርጊስ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የምክክር መድረኩ አሳታፊና አካታች መሆኑ ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ ምዕራፍ የሚያሸጋግር ታሪካዊ ክስተት ነው ። ምክክሩ ኢትዮጵያውያን ችግሮቻችንን በንግግርና በውይይት መፍታት እንድንችል በታሪክ የተገኘ መልካም አጋጣሚ ነው ሲሉም አመላክተዋል። ችግሮችን በምክክር፣ በውይይትና በእርቅ መፍታት የጥንት አባቶቻችንና እናቶቻችን ውጤታማ ባህል መሆኑን አሁናዊው ሂደት ዳግም አስመስክሯል ነው ያሉት። ይህም በአሁኑ ወቅት የሚስተዋሉ ዋልታ-ረገጥ ችግሮቻችንን በውይይት ፈትተን፣ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለች ሀገር ለማስረከብ ትልቅ አቅም የሚፈጥር እንደሆነም ነው የተናገሩት። ከሕዝብ የተወከሉ ዜጎች በዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ተመካክረው ማጠናቀቃቸው ዘላቂ ሰላምና አንድነትን የሚያጸና መሆኑን ተናግረዋል። ሌላው የጽሕፈት ቤቱ አባል ሃምሳ አለቃ ባለሟል መለሰ በበኩላቸው፤ የምክክር ሂደቱ ኢትዮጵያን ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረ ታሪካዊ ድል ተደርጎ የሚወሰድ እንደሆነም ገልጸዋል። ችግሮቻችንን በራሳችን ፍላጎትና አቅም መፍታት እንደምንችል ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት በተግባር ያረጋገጥንበት ነው ሲሉም አብራርተዋል። በአዲስ አበባ የተካሄደው ጉባኤ አካታችና አሳታፊ መሆኑ ለተመዘገበው ስኬት ዋና መሰረት እንደሆነም ነው የተናገሩት። "ምክክሩ አንዱ የሌላውን ሀሳብና ችግር ተጋርቶ፣ ተሳስቦና ተጋግዞ በአንድነት መኖር የሚያስችለው ነው" ያሉት ደግሞ ሌላው አባል ሃምሳ አለቃ አለማየሁ አበበ ናቸው። በቀጣይም የመመካከርና የመወያየት ባህላችንን በማስቀጠልና በማጎልበት ለዘላቂ ሰላማችንና አንድነታችን አስተማማኝ መሰረት መጣል አለብን ነው ያሉት። አስተያየት ሰጪዎቹ አያይዘውም፤ በአዲስ አበባ በተካሄደው ጉባኤ ሁሉም ተመካካሪ የወከለውን ሕዝብና አካባቢ ይጠቅማል ያለውን ሀሳብ በነፃነት በማንሸራሸር መግባባት ላይ መድረሱ መልካም ጅምር መሆኑን ተናግረዋል። በምክክር ጉባኤው ድምዳሜ ላይ የተደረሰባቸውን ውሳኔዎች መላው ሕብረተሰብ ተቀብሎ በመተግበር የሀገራችንን አንድነት ለማጽናት የድርሻችንን መወጣት አለብን ሲሉም ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያን ድል ያበሰረ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ
Aug 28, 2026 311
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ምክክሩ የኢትዮጵያን ድል ያበሰረ፣ ሕብረ ብሔራዊነትን የጠበቀ፣ አካታችና አሳታፊ ታሪካዊ ምዕራፍ መሆኑን በጉባኤው የተሳተፉ የዳያስፖራ ማህበረሰብ ተወካዮች ገለጹ። በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ከሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ ለአርባ ስድስት ቀናት ሲካሄድ የቆየው የኢትዮጵያ ዋናው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ በስኬት ተጠናቅቋል። በእንግሊዝ እና በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ የዳያስፖራ ማህበረሰብ የሕዝብ ወኪል ተመካካሪዎች ለኢዜአ እንዳሉት፤ የሀገራዊ ምክክር ሂደቱ አካታችና ተመካካሪዎች ሃሳባቸውን በነጻነት አንጸባርቀውበታል። በእንግሊዝ የሚኖሩ የዳያስፖራ ማህበረሰብ የሕዝብ ወኪል ተመካካሪ ኡስታዝ ሙክታር ጀማል እንዳሉት፤ ሀገራዊ ምክክሩ ሀገርን ወደ አዲስ ምዕራፍ ያሸጋገረና ኢትዮጵያ አሸናፊ የሆነችበት መድረክ ነው። ምክክሩ ዳያስፖራውን ጨምሮ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በተወካይ አማካኝነት የተሳተፈበት ተመካካሪዎች ሃሳባቸውን በነፃነት ያንፀባረቁበት ታሪካዊ መድረክ መሆኑንም ተናግረዋል። በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ የዳያስፖራ ማህበረሰብ የሕዝብ ወኪል ተመካካሪ ገዛኸኝ ሱማሞ በበኩላቸው፤ ምክክሩ የመነጋገር ባህልን የሚያዳብርና ሀገራዊ ድምፆች የተንፀባረቁበት ታሪካዊ መድረክ ነው ብለዋል። ሀገራዊ ምክክሩ የኢትዮጵያን ብዝሃነት የተንፀባረቀበትና ለመጪው ትውልድ የተሻለች ሀገር ማሻገር የሚያስችል ውጤታማ መድረክ መሆኑን ተናግረዋል። ሀገራዊ ምክክሩ ለዘላቂ ሰላም፣ የጋራ መግባባትና ዲሞክራሲ ስርዓት ግንባታ አስተዋፅኦ ያለው ጉባዔ መሆኑንም ገልጽዋል። ዳያስፖራው ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ትብብር ለማጠናከርና ልምዱን ለማካፈል ወርቃማ ዕድል የፈጠረ መሆኑንም ገልፀዋል።
የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ለይፋዊ የስራ ጉብኝት አዲስ አበባ ገቡ
Aug 28, 2026 323
አዲስ አበባ ፤ነሐሴ 22/2018 (ኢዜአ)፦ የታይላንድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉዋንግኬትክየው ለይፋዊ የስራ ጉብኝት እና ታሪካዊውን “የታይላንድ-አፍሪካ ኢኒሼቲቭ” በይፋ ለማስጀመር አዲስ አበባ ገብተዋል። ሚኒስትሩ ዛሬ ማለዳ አዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ብርሃኑ ጸጋዬ አቀባበል አድርገውላቸዋል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሲሃሳክ ፉዋንግኬትክየው በአዲስ አበባ ቆይታቸው ከመንግስት ከፍተኛ አመራሮች ጋር በሁለቱ ሃገራት ግንኙነት ዙሪያ ውይይት አንደሚያደርጉም ተገልጿል። ይህ ጉብኝት በኢትዮጵያ እና በታይላንድ መካከል እያደገ የመጣውን የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግርና የአፍሪካ-ታይላንድ ትብብርን የሚያጠናክር አዲስ ምዕራፍ ስለመሆኑም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ቀጣናዊ ትብብርና የጋራ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ያለመ የሕልውና ጥያቄ ነው
Aug 27, 2026 791
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ቀጣናዊ ትብብርና የጋራ ብልጽግናን ለማረጋገጠ ያለመ ፍትሐዊና የሕልውና ጥያቄ መሆኑን በኢፌዴሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ (ዶ/ር) ገለጹ። የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ ለኢዜአ እንዳሉት፤ የባሕር በር ለኢትዮጵያ ሰላምና ደኅንነት፣ ለኢኮኖሚ ዕድገት፣ ለቀጣናዊና ዓለም አቀፍ የንግድ ትብብር ጉልህ ስፍራ የሚሰጠው የህልውና ጉዳይ ነው። የኢትዮጵያን ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገትና የሕዝብ ቁጥር ታሳቢ በማድረግም ሀገርን ከታሪካዊ፣ ተፈጥሯዊ፣ መልክዓምድራዊና ሕጋዊ የባሕር በር ባለቤትነቷ ማስታረቅ ጊዜ ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ አይደለም ብለዋል። ስትራቴጂክ የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄም በትብብር ላይ የተመሰረተ ቀጣናዊ ሰላምና ደኅንነትን በማስጠበቅ የጋራ ዕድገትና ብልፅግናን የሚያሳልጥ የወጪና ገቢ ንግድን ለማሳለጥ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በተባበሩት መንግሥታት ጥናቶች መሠረት ወደብ አልባ ሀገራት ከባሕር በር ተጠቃሚ ከሆኑ ሀገራት ጋር ሲነጻጸሩ እስከ 25 በመቶ የሚደርስ የአጠቃላይ የሀገር ውስጥ ምርት ልዩነት እንደሚያጋጥማቸው ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ 95 በመቶ የሚሆነው ገቢና ወጪ ንግድ በአንድ ወደብ በኩል መከናወኑም ለሌሎች የልማት ሥራዎች ይውል የነበረው የውጭ ምንዛሬ እንደሚያስወጣ ተናግረዋል። ይህም በዓለም ንግድ ሥርዓት የወጪና ገቢ ተወዳዳሪነትን በማቀጨጭ በኢንዱስትሪ፣ ኢንቨስትመንትና በዜጎች ተጠቃሚነት ላይ ከፍተኛ ጫና እያሳደረ እንደሚገኝ አስረድተዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ ታሪካዊ መሠረትም ከሦስት አስርት ዓመታት በፊት ከአክሱም ዘመን ጀምሮ ለሺህ ዓመታት በአዱሊስ ወደብ አማካኝነት ከዓለም ጋር ሰፊ ግንኙነት ይደረግ እንደነበር አስታውሰዋል። በጂኦፖለቲካዊ አቀማመጥም ኢትዮጵያ ከቀይ ባሕር አቅራቢያ የተፈጠረች ሀገር መሆኗ በተፈጥሯዊና መልክዓምድራዊ አመክንዮ የተደገፈ ጥያቄ መሆኑን አስረድተዋል። በዓለም አቀፍ የባሕር ሕግጋትና የኢትዮጵያ የባሕር በር ያጣችበት ኢ-ሕጋዊ መንገድም የባሕር በር ባለቤትነት ጥያቄዋ ሕጋዊ መሠረት እንዳለው አስረጂ መሆኑን አብራርተዋል። በተባበሩት መንግሥታት የባሕር ሕግ ስምምነትና ሕግጋትም ወደብ አልባ ሀገራት ወደ ባሕር የመድረስና የመጠቀም መብታቸውን የሚደግፍ ድንጋጌና ማዕቀፍ መኖራቸውን አንስተዋል። አክለውም በቅርቡ በቱርክሜኒስታን አዋዛ ከተማ በተካሄደው የወደብ አልባ ታዳጊ ሀገራት ጉባኤ፣ በዚህ ዘርፍ ጉልህ ውሳኔዎች መወሰናቸውን ጠቁመው፣ የአዋዛ የፖለቲካ መግለጫም መጽደቁን አስታውሰዋል። የኢትዮጵያ የባሕር በር ፍላጎትም የግል ጥቅምን ብቻ ለማሳካት የቀረበ ሳይሆን የጋራ ቀጣናዊ ህልውናን በማስጠበቅ ትብብርንና የጋራ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ያለመ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። ኢትዮጵያም ይህንን አቋም ለጎረቤት ሀገራት በሁለትዮሽ እንዲሁም በተለያዩ መድረኮች በዲፕሎማሲያዊ መንገድ እያስረዳች መሆኑንም ጠቁመዋል።
ምክክሩ ኢትዮጵያውያን አለመግባባቶችን በሐሳብ የበላይነት መፍትሔ መስጠት እንደሚችሉ በተግባር የታየበት ነው
Aug 27, 2026 672
ወልቂጤ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦የምክክር ጉባኤው ኢትዮጵያውያን አለመግባባቶችን በሐሳብ የበላይነትና በጥበብ መፍትሔ መስጠት እንደሚችሉ በተግባር የታየበት መሆኑን የጉራጌ ዞን ነዋሪዎች ገለጹ፡፡ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤው ኢትዮጵያውያን በመግባባት ዘላቂ ሰላምን እውን ማድረግ የሚችሉት በኃይል አማራጭ ሳይሆን የሐሳብ የበላይነትን ባስቀደመ አካታች ውይይት ብቻ መሆኑን በተግባር ያሳየ አዲስ የፖለቲካ ምዕራፍ ነው። ተመካካሪዎቹ ልዩነቶቻቸውን በግልጽነት አቅርበው በጥበብና በመደማመጥ ለመፍታት ያደረጉት ጥረት፣ የሚነሱ አለመግባባቶችን በሰለጠነ መንገድ በውይይት መፍትሔ የመስጠት ልማድ እንዲዳብር መሠረትን ይጥላል። ነዋሪዎቹ እንደገለጹት፤ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤው ኢትዮጵያውያን አለመግባባቶችን በሐሳብ የበላይነት መፍትሔ መስጠት እንደሚችሉ በተግባር የታየበት ነው። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወይዘሮ ጥሩነሽ ምኑታ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያውያን በጋራ የመመካከርና የመወያየት ባህላቸውን በመጠቀም ውስጣዊ ችግሮቻቸውን በራሳቸው አቅም መፍታት እንደሚችሉ ጉባኤው ማሳየቱን ጠቅሰዋል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አቶ እስክንድር ነጋሽ ምክክሩ ኢትዮጵያውያን በራሳችን ጉዳዮች ላይ በመምከር የጋራ መፍትሔ መስጠት እንደምንችል ያስገነዘበ እንደሆነም አንስተዋል። የምክክር ጉባኤው በሐሳብ የበላይነት ላይ የተመሠረተ፣ በጠንካራ ሀገረ መንግሥት የጸናች ሃገርን በመገንባት ለትውልድ ለማስተላለፍ የሚያስችል መርህ የተከተለ እንደነበረም ጠቅሰዋል። ሀገራዊ ምክክሩ በኢትዮጵያ የቆዩ ችግሮችን በራሳችን አቅምና በጋራ ውይይት ለመፍታት የሚያስችል ታሪካዊ ዕድልን የፈጠረ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ አቶ ዳዊት ብርሃኔ ናቸው። ምክክሩ ቀጣይነት ያለው ሰላም፣ አንድነቱ የተጠበቀና በጽኑ መሠረት ላይ የተገነባ ሀገርን ለማንበር በሚደረገው ጥረት ውስጥ ወሳኝ ድርሻ እንዳለውም አመልክተዋል። ሀገራዊ የምክክር ጉባኤው በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ሕዝቡ እኩል እንዲመክርና እንዲወከል በማድረጉ ሀገራዊ ስሜትን ያነቃቃና ባለቤትነትን ያረጋገጠ መሆኑን የገለጹት ደግሞ አቶ ሃዲሞ ሃሰን ናቸው። ምክክሩ በሕዝቦች መካከል ያሉ የጋራ እሴቶችን በማጠናከር ረገድ ወደ ተሻለ አንድነት የሚያመጣ መሆኑን አውስተዋል።
በሰላም ማስከበር ዘርፍ የሚሰጡ ሥልጠናዎች ከአካዳሚክ እውቀት ባለፈ ተግባራዊ ክህሎትንና የላቀ ሙያዊ ስነ-ምግባርን ያገናዘቡ ናቸው -ሌተናል ጄኔራል ደሳለኝ ተሾመ
Aug 27, 2026 738
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦በሰላም ማስከበር ዘርፍ የሚሰጡ ሥልጠናዎች ከአካዳሚክ እውቀት ባለፈ ተግባራዊ ክህሎትንና የላቀ ሙያዊ ስነ-ምግባርን ያገናዘቡ ናቸው ሲሉ የመከላከያ ኢንስፔክተር ጄኔራል ቢሮ ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል ደሳለኝ ተሾመ ገለጹ። በአህጉሪቱ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን የጋራ ዓላማን አንግቦ መስራት ወሳኝ መሆኑንም የመከላከያ ሰላም ማስከበር ማዕከል ኃላፊ ሜጀር ጄኔራል አዳምነህ መንግሥቴ ገልፀዋል። የሰላም ማስከበር ስራዎች ስኬታማ እንዲሆኑ ከተለመደው ወታደራዊ ክህሎት ባለፈ የግጭቶችን ውስብስብ ባህሪ የሚረዱና ለውይይት ቅድሚያ የሚሰጡ ሙያተኞችን ማፈራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የመከላከያ ሰላም ማስከበር ማዕከል የዓለም አቀፍ ሰላም ማስከበር ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት በሰላምና ግጭት አፈታት አስተዳደር የሁለተኛ ዲግሪ ፕሮግራም የ3ኛ ዙር ተማሪዎቹን ዛሬ አስመርቋል። የመከላከያ ኢንስፔክተር ጄኔራል ቢሮ ኃላፊ ሌተናል ጄኔራል ደሳለኝ ተሾመ በዚሁ ጊዜ እንደተናገሩት፤ የስልጠናው ዋና ዓላማ በሰላም ማስከበር ሥራዎች ላይ የተሰማሩ ባለሙያዎችን አቅምና ሙያዊ ብቃት ማሳደግ ነው ብለዋል። እንዲሁም ከዓለም አቀፍ ደረጃዎችና መልካም ተሞክሮዎች ጋር የሚጣጣም እውቀትና ክህሎት ማስታጠቅ መሆኑንም ተናግረዋል። በዚህ ረገድ ኢንስቲትዩቱ የመከላከያ ሰራዊት አባላትን እና የተለያዩ ሀገራት ሠራዊት የዓለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች በብቃት መወጣት እንዲችሉ እያዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል። ተመራቂዎች በቆይታቸው ያገኙትን እውቀት ወደ ተግባር በመቀየር ሰላምን፣ ውይይትንና የሰዎችን ክብር የሚያስቀድሙ መሪዎች እንዲሆኑ አሳስበዋል። የመከላከያ ሰላም ማስከበር ማዕከል ኃላፊ ሜጀር ጄኔራል አዳምነህ መንግሥቴ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ በሰላም ማስከበር ዘርፍ የካበተ ረጅም ጊዜ ልምድ እንዳላት ተናግረዋል። ይህንን ልምድ ከዘመናዊ ቴክኖሎጂና አሰራር ጋር በማጣመር ብቁ ሰራዊት እየተገነባ ይገኛል ብለዋል። ማዕከሉ የሀገር ውስጥ አቅምን ከመገንባት ባለፈ ከአጋር ሀገራት ጋር አብሮ በመስራት ለአለም አቀፍ ሰላም የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የዓለም አቀፍ ሰላም ማስከበር ማሠልጠኛ ኢንስቲትዩት አዛዥ ኮሎኔል ጌቱ ታዬ፤ በመርሃ ግብሩ በበሰላም እና ግጭት አፈታት የሁለተኛ ዲግሪያቸውን ያጠናቀቁ ከኢትዮጵያና ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት የተወጣጡ 28 ተማሪዎች መሆናቸውን ተናግረዋል። ትምህርቱ በመከላከያ ሚኒስቴር፣ በጃፓን መንግስትና በተባበሩት መንግስታት የልማት ድርጅት ትብብር የሚሰጥ መሆኑን ጠቅሰው የሴቶችና የውጭ ሀገራት ተማሪዎች መካተት ለፕሮግራሙ ትልቅ ስኬት መሆኑን አብራርተዋል። ከተመራቂዎች መካከል ኮሎኔል ምትኩ ገመዳ እንደተናገሩት ኢትዮጵያ ለዓለም ሰላም የምታደርገውን አስተዋጽኦ አሁንም አጠናክራ እንደቀጠለች ጠቁመው ባገኙት እውቀት በተመደቡበት ማንኛውም ግጭት አፈታት ተልዕኮ ላይ ለመሰማራት ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሌተናል ኮሎኔል ኤልሳቤት አዳነ በበኩላቸው፤ በትምህርታቸው በወታደራዊ ዲፕሎማሲና በሰላም ግንባታ ዙሪያ ሰፊ እውቀት ማገኘታቸውንና ይህም በዓለም ደረጃ ያሉ የግጭት ሁኔታዎችንና የቅድመ-መከላከል ስልቶችን በግልጽ ለመረዳት እንዳስቻላቸው ገልጸዋል። ያገኙት እውቀት በሚሰሩት ስራ ላይ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብና በብቃት ለመስራት እንደሚያስችላቸው በመግለጽ በትግበራው ወቅት የተማሩትን ወደ ተግባር ለመቀየር መዘጋጀታቸውን የተናገሩት ደግሞ ኮማንደር እፁብድንቅ መርሻ ናቸው። ከውጭ ሀገር ሰልጣኞች መካከል ከዩጋንዳ የመጡት ዶክተር ደቪድ ኦኮሞ ሙኙዋ እንደተናገሩት፤ ኢንስቲትዩቱ ከተማሩባቸው በርካታ የዓለም ሀገራት ተቋማት መካከል ምርጡ እንደሆነ ገልጸዋል። በአካልና በኦንላይን የተቃኘው የትምህርት አሰጣጥ ዘዴው በጣም ውጤታማና የተቀናጀ እንደነበር መስክረዋል።
የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ከጋራ ተጠቃሚነትም ባለፈ ለቀጣናው ሰላም ወሳኝ ነው
Aug 27, 2026 689
ጅማ፤ ነሐሴ 21/2018ዓም(ኢዜአ) ፦ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከጋራ ተጠቃሚነትም ባለፈ የቀጣናውን ሰላም በአስተማማኝ መልኩ ለማስጠበቅ ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን ኢዜአ ያነጋገራቸው የዘርፉ ምሁራን ገለጹ። የአባይ መነሻ የሆነችውና ከቀይ ባህር በቅርብ እርቀት ላይ የምትገኘው ኢትዮጵያ ከሁለቱ ውሃዎች ጋር ህልውናዋ በእጅጉ የተቆራኘ መሆኑ ይታወቃል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ ከጋራ የልማትና ተጠቃሚነትም ባለፈ የአካባቢውን ሰላም በማስጠበቅ ረገድ ወሳኝና አስፈላጊ ሀገር መሆኗ ይታመናል። በጅማ ዩኒቨርሲቲ ቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት የውሀ ምህንድስና መምህር እና ተመራማሪ ማሙዬ ቡሴር (ረዳት ፕሮፌሰር)፤ ኢትዮጵያ የጂኦግራፊ እስረኛ ሆና መቀጠል የሌለባት በመሆኑ የባህር በር የግድ እንደሚያስፈልጋት ተናግረዋል። ከባህር በር ባለቤትነቷም ባሻገር የቀይ ባህርን ሰላም አስተማማኝ ለማድረግ የኢትዮጵያ አስፈላጊነት አማራጭ የሌለው መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጉዳይ ከጋራ ተጠቃሚነትም ባለፈ ለቀጣናው ሰላም መረጋገጥ ትልቅ አቅም የሚፈጥር መሆኑን አስረድተዋል። የቀጣናው አገራት በሁለቱ ውሃዎች ዙሪያ በትብብርና የጋራ ተጠቃሚነት መርህ ተቀራርበው መስራት እንዳለባቸው አንስተው ኢትዮጵያን ማእከል ያላደረገ ማንኛውም እንቅስቃሴ ውጤት ሊያመጣ አይችልም ብለዋል። የህዳሴ ግድብ የኢትዮጵያን የኃይል ልማት ፍላጎት መሰረት አድርጎ የተገነባ ቢሆንም በተለይም የጎረቤት አገራትን የሃይል ትስስርና የጋራ ተጠቃሚነትን መርህ ያደረገ መሆኑን አንስተዋል። በቀይ ባህርም በተመሳሳይ መርህ በትብብር መስራት የግድ መሆኑን ያነሱት ተመራማሪው በተናጠል የሚደረጉ የልማትም ይሁን የሰላምና ጸጥታ ጉዳዮች ውጤታማ ሊሆኑ አይችሉም ሲሉ ተናግረዋል። በዩኒቨርሲቲው የሃይድሮሊክስና የውሃ ሀብት ምህንድስና ትምህርት ክፍል መምህር ዋቅጅራ ታከለ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጉዳይ ከራሷ ጥቅም ባለፈ ሌሎች አገራትንም ተጠቃሚ ማድረግ የሚያስችል የልማት ትስስርን ይዞ የሚመጣ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም የቀይ ባህር ጉዳይ በትብብርና በሰላማዊ የዲፕሎማሲ አማራጭ መምራት እንደሚገባ አንስተው በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ እየተከተለችው ያለው መርህ የሚደነቅ ነው ብለዋል። በአምቦ ዩኒቨርሲቲ የህግ ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ብርሀኑ ሞሲሳ (ረዳት ፕሮፌሰር)፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጥያቄ በቅርበት፣ በመልካአ ምድርም ይሁን በዓለም አቀፍ ህግ አሳማኝና ተቀባይነት ያለው መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጉዳይ ከጋራ ተጠቃሚነትም ባለፈ የባህር ላይ ወንጀሎችን ለመግታትና ሽብርተኝነትን ለመታገል የሚያስችል ቀጣናዊ አቅም መሆኑን ገልጸዋል። በሰላም ማስከበርና ሽብርተኝነትን በመዋጋት ረገድ የኢትዮጵያ የመሪነት ሚና የሚታወቅ መሆኑን አንስተው፤ የኢትዮጵያ የባህር በር ባለቤትነት ጉዳይ ከጋራ ተጠቃሚነትም ባለፈ ለቀጣናው ሰላም መረጋገጥ ትልቅ አቅም የሚሆን ነው ብለዋል።
የምክክር ጉባኤው ችግሮችን በሰለጠነ መንገድ በውይይት ብቻ የመፍታት ባህልን ያጎለብታል
Aug 27, 2026 726
ሮቤ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ሀገራዊ ምክክሩ ችግሮችን በሰለጠነ መንገድ በውይይት ብቻ የመፍታት ባህል እንዲጎለብት ያደርጋል ሲሉ የሮቤ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። ሀገራዊ የምክክር ጉባኤው ለዘመናት በቆዩ ዘርፈ-ብዙ አለመግባባቶች ዙሪያ በመምከር በቀጣይ መሰል ውስብስብ ችግሮች እንዳይደገሙ ትልቅ የተግባርና የባህል ልምድ ጥሎ አልፏል። ከዚህም ዋነኛው የቱንም ያህል ጥልቅ እና ውስብስብ የሆኑ ሀገራዊ ቅሬታዎችና ልዩነቶች ቢኖሩ፣ ብቸኛውና ዘላቂው የመፍትሔ መንገድ የሐሳብ የበላይነትና በጠረጴዛ ዙሪያ የሚደረግ አካታች ውይይት ብቻ መሆኑን በተግባር ማረጋገጡ ነው። ሂደቱ ችግሮችን በኃይል ሳይሆን በሰለጠነ መንገድ በመደማመጥ እንዲሁም የችግሮች አካል ከመሆን ይልቅ የመፍትሔው ባለቤት በመሆን መፍታት እንደሚቻል ትልቅ ትምህርትን የሰጠ ነው ። በዚሁ ጉዳይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የሮቤ ከተማ ነዋሪዎች እንደገለፁትም፤ የምክክር ጉባኤው ችግሮችን በሰለጠነ መንገድ በውይይት ብቻ የመፍታት ባህልን ያጎለብታል። ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ ጫልቺሳ ዘውዴ፤ ጉባኤው ዜጎች በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እኩል እንዲመክሩና እንዲወከሉ በማድረግ ሀገራዊ ስሜትን ያነቃቃ እንዲሁም ለችግሮች መፍትሔ እንዲገኝ በር የከፈተ ነው ብለዋል። "ምክክሩ ችግሮች ምንም ያህል ጥልቅ እና ውስብስብ ቢሆኑም፣ በጠረጴዛ ዙሪያ በሰለጠነ መንገድ ተቀምጦ መፍትሔ ማግኘት እንደሚቻል ያሳየ ነው" ሲሉም አክለዋል። ሌላው የከተማዋ ነዋሪ አቶ ኢሳ ጣህር በበኩላቸው፤ ምክክሩ የቆዩ ቅሬታዎችን እና አለመግባባቶችን በሰለጠነ መንገድ መፍታት እንደሚቻል ትልቅ ትምህርትን የሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። ሐጂ አሬሪ ሀሰን የተባሉ ነዋሪ በበኩላቸው ሀገራዊ ምክክሩ በተለይ በታሪካችን ውስጥ የነበሩ ስብራቶችን ለማቃናት፣ ቅሬታዎችን ለመፍታትና የቆዩ ችግሮችን ለማስተካከል በውይይት የመፍታት ሰፊ ልምድን የሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።
የትግራይ ህዝብ በሕገ-ወጡ ሕወሓት የሚደርስበትን ግፍና መከራ ለማስቀረት ቡድኑ ላይ የጀመረውን ትግል ሊያጠናክር ይገባል
Aug 27, 2026 796
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ በትግራይ ክልል ሕዝብ ላይ ሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን የሚያደርሰውን ግፍና መከራ ለማስቀረት ሕዝቡ የጀመረውን ትግል አጠናክሮ በመቀጠል ተጠያቂነት እንዲሰፍን ማድረግ እንደሚያስፈልግ የሥምረት ፓርቲ የምክር ቤት አባልና የሚዲያና ኮሙኒኬሽን ምክትል ኃላፊ አቶ ጠዓመ ዓረዶም ገለጹ። አቶ ጠዓመ ዓረዶም በትግራይ ክልል ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ የሕገ-ወጡ ቡድን አፈሳና አፈና ከጥፋት አጋሩ ሻዕቢያ የተማረው የጥፋትና የጭቆና መንገድ ነው። በአሁኑ ወቅትም በኢትዮጵያ ከሚንቀሳቀሱ ጽንፈኛ ቡድኖች ጋር በመጣመር የሻዕቢያና የግብጽን ተልዕኮ ለማስፈጸም የኢትዮጵያን ሰላምና ደኅንነት ለማናጋት ትንኮሳ እያደረገ መሆኑን አስረድተዋል። በተለያዩ የአፋርና አማራ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች በሀገር መከላከያ ሰራዊት ላይ የሚፈጽመው ትንኮሳ ሀገርን በማተራመስ የትግራይ ክልልን ሕዝብ ለማጎሳቆል ያለመ መሆኑን ተናግረዋል። የትግራይ ክልል ሕዝብ እፎይታ የሰጠውን የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት በግልጽ በመናድ፣ በምንም ዓላማ ከማይዛመዱ ኃይሎች ጋር ያልተቀደሰ ጋብቻ በመፍጠር ሀገርን ለማተራመስ ሲፎክር እንደሚገኝ ገልጸዋል። አቶ ጠዓመ በማከልም፤ ሕገ-ወጡ ቡድን በበርካታ ወንጀልና ሰብዓዊ ግፍ የጨቀየ የዘራፊዎች ስብስብ መሆኑን ገልጸው፤ በአሁኑ ወቅትም በሚፈጽመው ከፍተኛ የዝርፊያና ምዝበራ ተግባር የሀገርን ሃብት እያሸሸ ነው ብለዋል። በትግራይ ክልል ሕዝብና ወጣቶች ላይ የሚፈጽመው ኢ-ሰብዓዊ እገታ፣ እስር፣ እንግልትና አፈና የሕዝብ ጉስቁልና ምንጭ የሆነ ስግብግብ ቡድን መሆኑን በተግባር እያስመሰከረ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ከግብጽና ሻዕቢያ በሚሰፈርለት የቅጥረኝነት ተልዕኮ ኢትዮጵያን በማተራመስ ከንቱ የህልም ቅዠቱን ለማሳካት እየጣረ መሆኑንም አብራርተዋል። የትግራይ ክልል ሕዝብና ወጣቶች የሕገ-ወጡን ቡድን የጥፋት ዓላማ አምርሮ በመታገል ሰላም፣ ልማትና አብሮነትን እንደሚሹ በይፋዊ ተቃውሟቸው ድምጻቸውን እያሰሙ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ለዚህም እናቶች፣ ወጣቶች እንዲሁም በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሚኖሩ የክልሉ ተወላጆች በቤተ-እምነቶችና በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን አማራጮች የቡድኑን እኩይ ሴራ እየኮነኑ መሆኑን ተናግረዋል። አቶ ጠዓመ እንዳሉት፣ ሕገ-ወጡ ቡድን ከሕዝብ የተነጠለ የወንጀለኞች ስብስብ ነው። መንግሥት የትግራይን ሕዝብ ጦርነት ከሚያደርስበት ጉስቁልና ለመታደግ የሰጠው ከፍተኛ ትዕግስት የሚደነቅ ነው ብለዋል። በቀጣይም በሕገ-ወጡ ቡድን በትግራይ ክልል ሕዝብ ላይ የሚደርሰውን ግፍና መከራ ለማስቀረት የሕግ የበላይነትን በማስከበር ተጠያቂነትን ማስፈን እንደሚኖርበት አስገንዝበዋል። የሕገ-ወጡ ሕወሓት ቡድን ጠባብ ስብስብ የትግራይ ክልል ሕዝብ ከኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ልማትና ሰላም ተቋዳሽ እንዳይሆን አበክሮ የሚሰራ ጸረ-ሕዝብ መሆኑን አስረድተዋል። በዚህም ፓርቲያቸው በትግራይ ክልል ሕዝብ ጫንቃ ላይ የተጫነውን ሕገ-ወጥ ስብስብ ለማስወገድ የጥፋት ቡድኑን የሴራ አጀንዳ የማጋለጥና የመበጣጠስ ሥራ እየሰራ እንደሚገኝ አንስተዋል። የትግራይ ክልል ሕዝብና ወጣቶች በቡድኑ ላይ የጀመሩትን ተቃውሞ በማቀጣጠል የጥፋት ቡድኑን ሕልም ማክሸፍ እንዳለባቸው መልዕክት አስተላልፈዋል።
የፀጥታ መዋቅሩ ከህዝቡ ጋር ተቀናጅቶ በመስራቱ የውስጥ ባንዳዎች እና የውጭ ባዳዎችን ሴራ አክሽፏል - ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል
Aug 27, 2026 736
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ)፦ የፀጥታ መዋቅሩ ከህዝቡ ጋር ተቀናጅቶ በመስራቱ የውስጥ ባንዳዎች እና የውጭ ባዳዎችን ሴራ ማክሸፍ መቻሉን የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል ገለጹ። የኢትዮጵያ ፖሊስ ኮሚሽነሮችና የሰላምና ፀጥታ ኃላፊዎች ሀገራዊ የጋራ የፀጥታ መድረክ እየተካሄደ ነው። ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረሚካኤል በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የፀጥታ መዋቅሩ ከህዝቡ ጋር በጋራ ተቀናጅቶ በመስራቱ ሰላምን የሚያጸኑ ውጤቶች ተገኝተዋል። ሰባተኛው ሀገራዊ ምርጫ በሰላም እንዲከናወን፣ በየደረጃው ያለው የፖሊስ ሰራዊት፣ የፀጥታና አስተዳደር ኃላፊዎች፣ ሚሊሻዎች፣ የሀገር መከላከያ ሰራዊት በጋራ በማቀድ መስራታቸውን አመልክተው፤ በዚህም በሀገርም ሆነ በዓለም በአርአያነት የሚጠቀስ ምርጫ በሰላማዊ መንገድ መካሄድ መቻሉን ተናግረዋል። ሁል ጊዜ ኢትዮጵያ በችግር እንድትቆይ ሰላሟን ለማናጋት የሚሹ የውስጥ እና የውጭ ጠላቶች በመገናኘት በርካታ ሴራዎችን እንደሚያቅዱ ያወሱት ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ፤ እነዚያን ሴራዎች በየደረጃው ህይወታቸውን ጭምር በመክፈል እና ሴራውን በማምከን፣ የሀገርን ሰላምና ደህንነት በማስጠበቅ ዛሬ ለተደረሰበት ደረጃ መሰራቱን ተናግረዋል። መድረኩ በቀጣይም የኢትዮጵያ ጠላቶች ሰላምና ደህንነት ለማናጋት ከውስጥ ባንዳዎች እና ከውጭ ባዳዎች ጋር ተገናኝተው የሚሰሩትን ሴራ ሁሉ ለማክሸፍ፣ ሰራዊቱ አሁንም ዝግጁ መሆኑን የሚያረጋግጥበት እና ለቀጣይ ተልዕኮዎች ራሱን የሚያዘጋጅበት ነው ሲሉም ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የቱሪስቶች መዳረሻ ከመሆን ባለፈ ትላልቅ የአህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ኹነቶች የሚካሄድባት ተመራጭ ሀገር መሆኗን አንስተዋል። የእነዚህ ኹነቶች በሰላም እና ያለምንም የፀጥታ ችግር እንዲከናወኑ የፖሊስ ሰራዊቱ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በጋራ ከፍተኛ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን አክለዋል። በቀጣይም ለሚካሄዱ ትላልቅ ሀገራዊ ኹነቶች በጋራ መወያየት፣ በጋራ ማቀድ እና በመዘጋጀት የጠላትን ሴራ እያከሸፍን በሰላም እንዲካሄዱ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። የዛሬው መድረክም በዋናነት የተከናወኑትን ሥራዎች እና በእዚያ ውስጥ የተገኙ ጥሩ ተሞክሮዎች እና ያጋጠሙን ክፍተቶች በመለየት በቀጣይ ደግሞ ለሚኖር ተልዕኮ ከወዲሁ ለመዘጋጀት ያለመ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ ጠላቶችን ሴራ በማክሸፍና የሀገሪቱን ብልጽግና እውን ለማድረግ የሚከናወኑ ተግባራት ውጤታማ እንዲሆኑ የጋራ ስራችንን ልናጠናክር ይገባል ብለዋል።