ፖለቲካ
የኢትዮጵያ የዓለም የዲፕሎማሲ ስብት ማዕከልነት እየጨመረ መጥቷል
Apr 27, 2024 18
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የዓለም የዲፕሎማሲ ስብት ማዕከልነት እየጨመረ መምጣቱን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ ተናገሩ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር 37ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ እና 44ኛው የአፍሪካ ሕብረት የሥራ አስፈፃሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት እውቅና ሰጥቷል። በመርሃ ግብሩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ እና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት ስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ስብሰባው "ለ21ኛው ክፍለ ዘመን የሚመጥን አፍሪካዊ ማስተማር፤ የማይበገሩ የትምህርት ስርዓቶች በመገንባት በአፍሪካ ሁሉን አቀፍ፣ የሕይወት ዘመን ጥራትና አግባብነት ያለው የትምህርት ተደራሽነትን ማስፋት" በሚል መሪ ሃሳብ መካሄዱ ይታወሳል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አምባሳደር ታዬ አጽቀሥላሴ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ኢትዮጵያ የዓለም የዲፕሎማሲ ስብት ማዕከልነቷ እየጨመረ መጥቷል። የሀገሪቱ የገጽታ ግንባታ ላይ በተሰራ ስራና ቀደም ሲል በነበራት አኩሪ ታሪክ በዓለም የዲፕሎማሲ ስብት ማዕከልነቷ እያደገ መጥቷል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ነጻነትና አንድነት ላበረከተችው አስተዋጽኦ የአፍሪካ መዲና ለመሆን በቅታለች።   የቀደሙ የኢትዮጵያ መሪዎች በሰሩት ጠንካራ የዲፕሎማሲ ስራ የሕብረቱ መቀመጫ አዲስ አበባ ሊሆን ችሏል ብለዋል። የተወሰኑ ሀገራት በተለያዩ ጊዜያት የሕብረቱን መቀመጫ ወደ ሌላ ሀገር ለማዛወር ያደረጉት ጥረት በኢትዮጵያ መሪዎች ጠንካራ የዲፕሎማሲ ስራ ሳይሳካ መቅረቱን አስታውሰዋል።   በ37ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጉባኤው በስኬት እንዲጠናቀቅና የኢትዮጵያ ከፍታ እንዲጨምር ላደረጉት አስተዋጽኦ ምስጋና አቅርበዋል። በቀጣይም የበለጠ በቅንጅት በመስራት እንግዳ ተቀባይነታችንን ለዓለም እያስመሰከርን መቀጠል አለብን ብለዋል።   የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ብርቱካን አያኖ በዚሁ ጊዜ፤ 37ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ እና 44ኛው የአፍሪካ ሕብረት የሥራ አስፈፃሚ ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ በከፍተኛ ቅንጅት በስኬት መጠናቀቁን አስታውሰዋል። በሕብረቱ ስብሰባ ከ8 ሺህ በላይ እንግዶች ተሳትፈው በሰላም ወደ ሀገራቸው መመለሳቸውንም ገልጸዋል። ለዚህም የብሔራዊ አስተባባሪ ኮሚቴ፣ የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች፣ የጸጥታ አካላት፣ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ስብሰባው በስኬት እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ተናግረዋል።    
ሴቶች በሀገራዊ ምክክር ሂደት የነቃ ተሳትፎ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል -ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ
Apr 27, 2024 56
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 19/2016(ኢዜአ)፡- ሴቶች በሀገራዊ ምክክር ሂደት የነቃ ተሳትፎ በማድረግ የሀገረ መንግስት ግንባታው ውጤታማ እንዲሆን ሚናቸውን ሊወጡ ይገባል ሲሉ የኢፌዲሪ ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ አስታወቁ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የሴቶችን ተሳትፎ ለማጉላት "አገራዊ ምክክር ለአንቺ፤ ስለኢትዮጵያ በአንቺ፤ ኢትዮጵያ እየመከረች ነው" በሚል መሪ ሀሳብ የምክክር መድረክ በማካሄድ ላይ ይገኛል። ፕሬዝዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ አካታች ሀገራዊ ምክክር ማካሔድ ብሔራዊ መግባባትን የመፍጠር እና ተቀራርቦ የመስራት ባህልን ለማጎልበት ጉልህ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል። በብሔራዊ ምክክር ያለፉ አገራት በጦርነት ከሚገኝ ጊዜያዊ መፍትሔ ይልቅ ለንግግርና ምክክር ቅድሚያ በመስጠታቸው ዘላቂ ሰላምን በመፍጠር የተሻለ ኢኮኖሚ እየገነቡ እንደሚገኙ ተናግረዋል።   በኢትዮጵያ እየተካሄደ የሚገኘው ሀገራዊ ምክክር የተሻለ ሀገር ለመገንባት ዘርፈ ብዙ ፋይዳ ስላለው ሴቶች ገንቢ ተሳትፏቸውን ለማበርከት መዘጋጀት እንደሚኖርባቸው አስገንዝብዋል። በኢትዮጵያ በሚፈጠሩ አለመግባባቶች እና የሃሳብ ልዩነቶች ሴቶች ግንባር ቀደም የጉዳት ሰለባ መሆናቸውን አንስተዋል። ለዚህም በሀገረ መንግስት ግንባታ የሴቶች ተሳትፎ ወሳኝ በመሆኑ በሀገራዊ ምክክር ሂደት ላይ ወሳኝ ተሳትፏቸውን ማጉላት እንደሚኖርባቸው አሳስበዋል። ስልታዊ መፍትሔን በማበጀት ረገድ ሴቶች የተሰጣቸው ተፈጥሯዊ ፀጋ የላቀ በመሆኑ ምክክሩ ላይ የሚያደርጉት ተሳትፎ ቀላል የሚባል እንዳልሆነም አብራርተዋል። በሀገራዊ ምክክሩ ላይ የሴቶች ድምፅ ትልቅ ቦታ እንደሚሰጠው በማመን በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች ያሉ ሴቶች የነቃ ተሳትፎ ሊያደርጉ እንደሚገባ ጥሪ አቅርበዋል።  
በዕቅድ መመራት ካልቻልን ለህዝቡ የገባነውን ቃል ማሳካት አንችልም - አቶ ሽመልስ አብዲሳ
Apr 27, 2024 50
አዳማ፤ ሚያዝያ 19/2016(ኢዜአ)፦በዕቅድ መመራት ካልቻልን ለህዝቡ የገባነውን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ቃል አናሳካም ሲሉ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ። በክልል ያለፉት ዘጠኝ ወራት የመንግሥትና የፓርቲ የስራ አፈፃፀም ክንውንና የ2017 ዓ.ም መነሻ ዕቅድ ላይ ያተኮረ ግምገማ በአዳማ አባገዳ አዳራሽ በመካሄድ ላይ ይገኛል ። በመድረኩ ላይም አቶ ሽመልስ እንደገለጹት በዕቅድ መመራት ካልተቻለ ለህዝቡ የተገባውን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ የልማት ስራዎችን ማሳካት አይቻልም ብለዋል። እቅዱ የሚሳካው በተሰጠው አቅጣጫ በአግባቡ ሲተገበር መሆኑን ገልጸው ከዚህ አኳያ የተሰጠ አቅጣጫ ቆጥሮ በመቀበል ያለመተግበር ክፍተቶች እንዳሉም ጠቁመዋል። የልማት፤ የሰላም፣ የአገልግሎትና መልካም አስተዳደር ውጤቶች የምዘና ዝንባሌ በትንሽ ድሎች መዘናጋት እየፈጠረ ነው ያሉት አቶ ሽመልስ ከዚህ አስተሳሰብና ተግባር መውጣት አለብን ሲሉም አሳስበዋል። የ2017 ዓ.ም ዕቅድም በዚህ መልኩ መፈፀም እንደማይቻል ገልጸው መድረኩ አመራሩ የእቅዱን ማስፈፀሚያ ስልቶች በሚገባ ወደ መሬት ለማውረድ የሚያስችል አቅጣጫ የሚቀመጥበት መሆኑንም ተናግረዋል።   በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ በበኩላቸው መድረኩ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ለህዝቡ የተገባውን ቃል እውን ከማድረግ አኳያ የታዩ ጥንካሬና ድክመቶችን በመለየት ቀጣይ አቅጣጫ ለማስቀመጥ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም በየአካባቢው የሚገኙትን አቅሞችና አማራጮች በመለየት ለዕቅዱ ውጤታማነት የምንጠቀምበት ነው ሲሉም አስረድተዋል። ፓርቲው ለህዝቡ የገባውን ቃል ከማሳካት፣ ጽንፈኝነትን ከመታገልና አስተማማኝ ሰላም ከማስፈን እንዲሁም የተዛቡ አመለካከቶችን ከማረም ጀምሮ ጠንካራ የአሰራር ስርዓት በመዘርጋት የሚሰራበት መሆኑንም አስረድተዋል።   ጠንካራ ድርጅታዊ ቁመና መፍጠር ውስጣዊ ትግላችንን ማጠናከር ነው ያሉት አቶ ፍቃዱ ሰላምን ማስፈን ፣ልማትና መልካም አስተዳደርን ማረጋገጥና አገልግሎት አሰጣጥን ማሻሻል የሚፈትሽበት ነው ብለዋል። መድረኩ ያለፉት ዘጠኝ ወራት የመንግስትና የፓርቲ ስራ ክንውን፣ ጠንካራና ደካማ ጎኖች እንዲሁም የ2017 ዓ.ም የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት ማስፈፀሚያ የመነሻ ዕቅድ ቀርቦ ምክክር ይካሄድበታል ተብሏል።
የአማራ ክልል ከፍተኛ ልዑክ በዋሽንግተን ዲሲ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ ዲፕሎማቶች ጋር ምክክር አደረገ
Apr 27, 2024 61
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2016 (ኢዜአ)፡- ወደ ሰሜን አሜሪካ የሥራ ጉዞ ያደረገው የአማራ ክልል ከፍተኛ የልዑካን ቡድን በዋሽንግተን ዲሲ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ አምባሳደር እና ዲፕሎማቶች ጋር ምክክር አደረገ። ልዑኩ በተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች በመዘዋወር ከኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ ከልዩ ልዩ ኩባንያዎች፣ ከዩኒቨርስቲዎች እንዲሁም ከተለያዩ ተቋማትና አካላት ጋር ውይይት እና ምክክር አድርጓል። በዋሽንግተን ዲሲ ከኢትዮጵያ ኤምባሲ ጋር የተደረገው ውይይት ደግሞ መንግሥትና ኤምባሲው ማከናወን ስለሚገባቸው ቀጣይ ሥራዎች ላይ ያተኮረ እንደሆነ ተገልጿል።   በአሜሪካ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ባለ ሙሉ ስልጣን አምባሳደር ዶክተር ኢንጅነር ስለሺ በቀለ እና ዲፕሎማቶች ከልዑካን ቡድኑ ጋር ባደረጉት ምክክር፥ የተሠራው ሥራ ውጤታማ እንደነበር ገልጸው፤ በቀጣይም ከዚህ የተሻለ ውጤት ማስገኘት የሚያስችሉ ሥራዎችን ለመሥራት እንደ መነሻ ሆኖ ያገለግላል ብለዋል። በብልጽግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ይርጋ ሲሳይ እና በምክትል ርእሰ መሥተዳድር ማዕረግ የከተማ ልማት ዘርፍ አስተባባሪ እና የከተማ እና መሰረተ ልማት ቢሮ ኅላፊ ዶክተር አህመዲን መሐመድ በኢትዮጵያ እየተካሄደ ያለውን ሪፎርም እንዲሁም ወቅታዊ የሀገሪቱን እና የክልሉን ሁኔታ በተመለከተ ለዲፕሎማቶች መረጃ እና ማብራሪያ ሰጥዋል። የልዑካን ቡድኑ በአሜሪካ በነበረው ቆይታ ለኢትዮጵያ ጠቃሚ የሆኑ ተግባራትን ማከናወኑን አውስተው በቀጣይ ከዚህ ጉዞ የተገኙት ተሞክሮዎች ተቀምረው ከትውልደ- ኢትዮጵያውያን እና ኢትዮጵያውያን ጋር የሚደረጉ ውይይቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ መናገራውን ከዋሽንግተን ዲሲ የኢትዮጵያ ኤምባሲ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
37ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት እውቅና ተሰጠ
Apr 26, 2024 71
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር 37ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ እና 44ኛው የአፍሪካ ሕብረት የሥራ አስፈፃሚ የምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት እውቅና ሰጠ። በመርሃ ግብሩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ታዬ አጽቀሥላሴ፣የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ብርቱካን አያኖ ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት ስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል። ስብሰባው"ለ21ኛው ክፍለ ዘመን የሚመጥን አፍሪካዊ ማስተማር፤ የማይበገሩ የትምህርት ስርዓቶች በመገንባት በአፍሪካ ሁሉን አቀፍ፣የሕይወት ዘመን ጥራትና አግባብነት ያለው የትምህርት ተደራሽነትን ማስፋት“ በሚል መሪ ሃሳብ መካሄዱ ይታወሳል።   የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ብርቱካን አያኖ በዚሁ ጊዜ ፤37ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባኤ እና 44ኛው የአፍሪካ ሕብረት የሥራ አስፈፃሚ የምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ በከፍተኛ ቅንጅት በስኬት መጠናቀቁን አስታውሰዋል ። በሕብረቱ ስብሰባ ከ8 ሺህ በላይ እንግዶች ተሳትፈው በሰላም ወደ አገራቸው መመለሳቸውን ገልጸዋል። ለዚህም የብሔራዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ፣የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች፣የጸጥታ አካላት ፣የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ስብሰባው በስኬት እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን ተናግረዋል። ይህም የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅሞች ለማስከበር የሚያስችሉ የተለያዩ ስራዎች እንዲከናወኑ ማድረግ አስችሏል ብለዋል።  
በተቋማት የሚታዩ ብልሹ አሰራርና የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዲፈቱ በሚዲያ ተቋማቱ ቅርንጫፎች የተጀመሩ የይዘት ሥራዎች መጠናከር አለባቸው
Apr 26, 2024 101
አዳማ፤ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፡- በተቋማት የሚታዩ ብልሹ አሰራርና የመልካም አስተዳደር ችግሮች እንዲፈቱ በሚዲያ ተቋማቱ ቅርንጫፎች የተጀመሩ የይዘት ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸው በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴና የአመራር አባላት የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት አዳማ ቅርንጫፍና የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን አዳማ ማሰራጫ ጣቢያን ጎብኝተዋል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ እውነቱ አለነ በዚህ ወቅት እንደገለፁት አዳማ ከአዲስ አበባ ቀጥላ ሁለተኛዋ የቱሪዝምና ኮንፈረንስ ከተማ መሆኗን ጠቅሰዋል። በሚዲያ ተቋማቱ ቅርንጫፎች እየተከናወኑ ያሉት ኩነቶችና የፕሮጀክት ስራዎች የዋናው መስሪያ ቤትን ጫና ከመቀነሳቸው በተጓዳኝ ለህብረተሰቡም የቀረቡ ናቸው ብለዋል። በተለይም የዴሞክራሲ ተቋማት በምልከታና በዳሰሳ ጥናት የሚያገኙትን ግኝቶች ከኩነት ባለፈ የፕሮጀክት ስራዎችን በመስራት ረገድ የቅርንጫፎቹ ሙያተኞች እያከናወኑ ያሉትን አበረታች ተግባር አጠናክረው መቀጠል አለባቸው ብለዋል። የዞኖችና የከተማ አስተዳደሮችን ብልሹ አሰራርና የመልካም አስተዳደር እጦት ችግሮችን ከመፍታት አንጻር እየተሰሩ ያሉ የይዘት ስራዎች በቀጣይም ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ነው ያሉት። ቅርንጫፎቹ ከዋናው መስሪያ ቤት ጋር በቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ያላቸው ትስስር፣ የዜና ቅብብሎሽና ቅንጅታዊ ስራ ይበልጥ መጠናከር ይገባዋል ብለዋል። የቋሚ ኮሚቴው አባልና የሚዲያ ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ አቡኔ ዓለም በበኩላቸው የኢዜአ አዳማ ቅርንጫፍ ከቢሮ አደረጃጀት ጀምሮ ጥሩ ይዘት ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ቅርንጫፉ ከዕለታዊ ኩነቶች ባለፈ በከተማዋ በሚካሄዱ ሀገራዊና ክልላዊ መድረኮች የሀገሪቷን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ስኬቶች፣ ውስንነቶችና የቀጣይ ትኩረትን መሰረት ያደረጉ የፕሮጀክትና የዕቅድ ሥራዎች ማከናወኑን በጥሩ ጎን ተመልክተናል ብለዋል። በተለይም በአዳማ የሚካሄዱ ሀገራዊና ክልላዊ ሥራዎች ቅርንጫፉ የሚሸፍናቸውና ከዋናው መስሪያ ቤት የጊዜ፣ የትራንስፖርትና የወጪ ጫናዎችን የቀነሰ መሆኑን ገልጸዋል። ቅርንጫፉ በአካባቢው ካሉ ሌሎች ሚዲያዎች ጋር ያለውን ትስስር ማጠናከር አለበት ያሉት ወይዘሮ አቡኔ፤ በዙሪያው ባሉ አካባቢዎችም ተንቀሳቅሶ ሽፋን መስጠት እንዳለበት አሳስበዋል። የቋሚ ኮሚቴው አባላትና የአመራር አካላቱ በተመሳሳይ የኢቲቪ የአዳማ ቅርንጫፍ የማሰራጫ ጣቢያን የተመለከቱ ሲሆን ጣቢያው ጥራትና ተደራሽነት ላይ በትኩረት መስራት እንዳለበት አመልክተዋል።    
የኢትዮጵያና ጅቡቲ የሚኒስትሮች የጋራ ኮሚሽን ስብሰባ የሁለቱን አገራት ግንኙነት ይበልጥ በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ላይ በመምከር በስምምነት ተጠናቀቀ
Apr 26, 2024 73
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 18/2016(ኢዜአ)፦ ለሁለት ቀናት በጅቡቲ ሲካሄድ የቆየው የኢትዮጵያና ጅቡቲ የሚኒስትሮች የጋራ ኮሚሽን ስብሰባ የሁለቱን አገራት ግንኙነት ይበልጥ በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ላይ በመምከር በስምምነት መጠናቀቁ ተገለጸ፡፡ የጁቡቲው ፕሬዝዳንት እስማኤል ኡመር ጊሌ ወደ ኢትዮጵያ በመጡበት ወቅት አገራቱን በውኃ፣ በፈጣን መንገድ፣ ሃይል አቅርቦት፣ ወደብ አገልገሎት እንዲሁም አጠቃላይ በሎጂስቲክስ ዘርፉ ማስተሳሰር በሚቻልበት ጉዳይ ላይ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጋር መምክራቸው ይታወቃል፡፡ ኢትዮጵያና ጅቡቲ ረዥም ዘመናትን ያስቆጠረ ታሪካዊ ወዳጅነት ያላቸው ሲሆን፤ የአገራቱ ወዳጅነት በህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ጭምር የተሳሰረ ነው፡፡ የሁለቱ ሀገራት መሪዎችም የአገራቱን ታሪካዊ ግንኙነት በበርካታ መስኮች ለማጠናከር በጋራ እየሰሩ ይገኛሉ፡፡ የአገራቱን ግንኙነት በማሳለጥ ረገድ የኢትዮጵያና ጅቡቲ የሚኒስትሮች የጋራ ኮሚሽን ሚናው ከፍተኛ ሲሆን፤ የጋራ ኮሚሽኑ በጅቡቲ ለሁለት ቀናት ሲያካሂድ የቆየውን ስብሰባ አጠናቋል፡፡ ስብሰባውን የኢፌዴሪ ትራንስፖርት እና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር ዶክተር አለሙ ስሜ እና የጅቡቲ የመሰረተ ልማት ሚኒስትር ሀሰን ሁመድ ኢብራሂም በጋራ መርተውታል፡፡ በስብሰባው በ16ኛው የኢትዮ-ጅቡቲ የሚኒስትሮች የጋራ ምክክር መድረክ ላይ ስምምነት የተደረሰባቸውን ጉዳዮች፣ በስምምነቱ ወቅት በሁለቱም ወገን ክትትል ተደርጎባቸው መፍትሄ እንዲሰጥባቸው አቀጣጫ የተሰጠባቸው ጉዳዮችን የአፈጻጸም ሂደት ተገምግሟል፡፡ በሁለቱ አገራት ሁሉን አቀፍ የትብብር ማዕቀፎች፣ በኢንቨስትመንትና በህገ-ወጥ የጠረፍ ንግድ፣ በሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር፣ በትራንስፖርት እና ሎጅስቲክ ዘርፎች በተለይም በዲኪል-ጋላፊ መንገድ ግንባታ አፈፀፃም ላይም ውይይት ተደርጓል፡፡ የመንገድ ፈንድ ክፍያ፣ የወደብና ትራንዚት እንዲሁም በጉምሩክ አገልግሎት አሰጣጥ ዙሪያ ያሉ ማነቆዎች ለመፍታት እየተደረጉ ባሉት ጥረቶች ላይ ምክክር መደረጉም ነው የተገለጸው፡፡ በዚሁ መነሻነት አገራቱ ከዚህ ቀድም የተፈራረሙት የወደብ እና ትራንዚት አገልግሎቶች፣ የጉምሩክ ፕሮቶኮል ስምምነት እና የመልቲሞዳል ስምምነቶች ለማሻሻል የቴክኒክ ኮሚቴዎች መዋቀሩ ተገልጿል። በመጪው ሐምሌ 2016 ዓ.ም. ጅቡቲ በሚካሄደው 17ኛው የሚኒስትሮች የጋራ ምክክር መድረክ የሚሆኑ የትኩረት አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ መድረኩ በስምምነት ተጠናቋል። የትራንስፖርት እና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር ዶክተር አለሙ ስሜ በዚሁ ጊዜ ባደረጉት የማጠቃለያ ንግግር ኢትዮጵያ እና ጅቡቲ ለረዥም ጊዜ የቆየ የጠበቀ ወዳጅነት ያላቸው አገሮች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡   በስብሰባው የተቀመጡ አቅጣጫዎች ተፈጻሚነት አገራቱ በቁርጠኝነት እንደሚሰሩም ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡ በተለይም በሁለቱ አገራት መካካል ያለውን የሎጅስቲክስ ትስስር ይበልጥ ለማጠናከር በትኩረት መስራት እንደሚገባ አመላክተዋል፡፡ የጅቡቲ የመሰረተ ልማት ሚኒስትር ሀሰን ሁመድ ኢብራሂም በበኩላቸው የኢትዮጵያንና የጁቡቲን የሁለትዮሽ ግንኙነት ለማጠናከር መሰል መድረኮች ትልቅ አስተዋዕጾ እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡   ስብሰባውም የጋራ መግባባት የሰፈነበት እንደነበር ጠቁመዋል፡፡ ለሁለት ቀናት በጅቡቲ በተካሄደው የኢትዮጵያና ጅቡቲ የሚኒስትሮች የጋራ ኮሚሽን ስብሰባ ላይ የትራንስፖርት እና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር ዶክተር አለሙ ስሜን ጨምሮ የገቢዎች ሚኒስትር አይናለም ንጉሴ፣ የጉምሩክ ኮሚሽነር ደበሌ ቃበታ እንዲሁም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊዎች፣ ዲፕሎማቶች ተሳትፈዋል፡፡ በጅቡቲ ወገን ደግሞ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማህሙድ አሊ ዩሱፍ፣ የመሠረተ-ልማት ሚኒስትር ሀሰን ሁመድ ኢብራሂም፣ የግብርና ሚኒስትር መሀመድ አህመድ አወሌ እንዲሁም የአገሪቷ የጉምሩክ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል፡፡
ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከብልሹ አሰራር ጋር በተያያዘ በ244 ሰራተኞች ላይ እርምጃ ተወስዷል - የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት
Apr 26, 2024 112
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2016(ኢዜአ)፡- ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከብልሹ አሰራር ጋር በተያያዘ በ244 ሰራተኞች ላይ እርምጃ መወሰዱን የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት አስታወቀ። አገልግሎቱ ይህን ያለው የዘጠኝ ወር የስራ አፈፃፀሙን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ለህግና ፍትህ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሲያቀርብ ነው። አገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን ለዜጎች ጥያቄ ፈጣንና ቀልጣፋ ምላሽ ለመስጠት የተለያዩ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ተቋሙ ገልጿል።   በተለይም ከደላሎች ጋር በመመሳጠር ህገ-ወጥ ተግባር ላይ ተሰማርተው በተገኙ 244 ሰራተኞችና 30 ህገ-ወጥ ደላሎች ላይ ከጸጥታ አካላት ጋር በመተባበር እርምጃ መወሰዱን በሪፖርቱ አመላክቷል። በሌላ በኩል በተለያየ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ገብተው ባልተፈቀደላቸው የስራ መስክ በተሰማሩና ህጋዊ ሰነድ ባላሟሉ የውጭ ዜጎች ላይ ቅጣት ተጠሎባቸው ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ መደረጉ ተነግሯል።
የፀጥታ ኃይሉ አቅም እየተጠናከረ በመምጣቱ የሠላም ሁኔታው መሻሻል አሳይቷል
Apr 25, 2024 141
  አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 17/2016 (ኢዜአ)፦ የባህርዳር ጎንደር ኮማንድ ፖስት የደቡብ ጎንደር ዞን የደብረ ታቦር ከተማ አስተዳደር የፀጥታ ኃይሉ አቅም እየተጠናከረ በመምጣቱ የሠላም ሁኔታው መሻሻል ማሳየቱ ገለጸ። በባህርዳር ጎንደር ኮማንድ ፖስት ደቡብ ጎንደር ዞን የደብረ ታቦር ከተማ አስተዳደር አሁናዊ የፀጥታ ሁኔታውን አስመልክቶ ከከተማ አስተዳደሩ የፀጥታ ኃይል ጋር ውይይት አድርጓል። አጠቃላይ የከተማውን የፀጥታ ሁኔታና የተልዕኮ አፈፃፀም እንዲሁም የተልዕኮ አፈፃፀሙ እያስገኘ ባለው ውጤትና በቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ነው ውይይት ያካሄደው።   በአካባቢው ተልዕኮ በመፈፀም ላይ የሚገኘው ክፍለጦር አዛዥና የኮማንድ ፖስቱ አስተባባሪ ኮሎኔል ሻምበል አስማማው እንደገለጹት ኮማንድ ፖስቱ ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት የዞን፣ የወረዳና የቀበሌ የፀጥታ ኃይሎችን አቅም ማጠናከር፣ በራስ አቅም ግዳጅ መፈፀምና የቀጠናውን ሠላም ማረጋገጥ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የባህርዳር ጎንደር ኮማንድ ፖስት አስቀምጦት የነበረው የአፈፃፀም አቅጣጫ የተሻለ ነው ብለዋል። ኮሎኔል ሻምበል አስማማው የሠራዊቱን ምት መቋቋም ተስኖት የተበተነውን ፅንፈኛ የማደን ስራ በተጠናከረ መንገድ እየፈፀመ መሆኑን ጠቁመው የፀጥታ ኃይሉ ደግሞ አካባቢውን በሚገባ በራሱ አቅም መጠበቅና ሠላሙን ማጠናከር እንደሚገባው አሳስበዋል።   የደብረ ታቦር ከተማ ከንቲባ አቶ ደሴ መኮንን በበኩላቸው አሁናዊ የከተማ አስተዳደሩና የአካባቢው የፀጥታ ሁኔታ መሻሻል የታየበት መሆኑንና የፀጥታ ኃይሉ ራሱን ችሎ አካባቢውን በንቃት ለመጠበቅ የሚያደርገው ጥረትም አበረታች ነው ብለዋል። አቶ ደሴ መኮንን ኮማንድ ፖስቱ ያስቀመጠውን የአፈፃፀም አቅጣጫ ተግባራዊ ለማድረግ አቅማችንን የበለጠ ማጠናከር ይግባናል ብለዋል። በዚህም የተገኘውን ውጤት ለማስቀጠል ሁሉም የፀጥታ ኃይል ኃላፊነቱን በቁርጠኝነት ሊወጣ እንደሚገባውም መግለጻቸውን ከመከላከያ ሰራዊት የተገኘው መረጃ ያመለክታል። የከተማው የኮማንድ ፖስት አባል ሻለቃ ጭፍራው አሰፋ በበኩላቸው የከተማው ፖሊስ፣ ሚሊሻ፣ ሠላም አስከባሪና የአድማ ብተና ኃይሉ ከሠራዊቱ ጋር በቅንጅት እየሰሩ መሆኑን ገልጸው፤ የሠላም ሁኔታውም ከፍተኛ መሻሻልን እያሳየ መሆኑን ጠቅሰዋል።
ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤት በወቅታዊ ሀገራዊ የደህንነት እና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ ያወጣው መግለጫ የያዛቸው አንኳር ነጥቦች፦
Apr 25, 2024 132
ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤት በወቅታዊ ሀገራዊ የደህንነት እና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ ያወጣው መግለጫ የያዛቸው አንኳር ነጥቦች፦ ሀገራዊ ምክክር ሂደትን በሚመለከት የኢትዮጵያ ችግር የአሁኑን አካሄድ በማስተካከል ብቻ አይፈታም፤ በታሪክ ውስጥ የወረስናቸውን ስብራቶች መጠገንም የግድ ይለናል፤ እነዚህን ስብራቶች ነባሩን ፖለቲካዊ ችግር በሀገራዊ ምክክር መፍታት፤ የቅርብ ዘመናችንን የፖለቲካ ችግር ደግሞ በሽግግር ፍትሕ እና በተሐድሶ ማረም፤ በኢትዮጵያ ተጨባጭ ሁኔታ አንድ መንግሥት በምርጫ አሸንፎ ሥልጣን ቢይዝም እንኳን ብቻውን ሊወስናቸው የማይገቡ፣ ሀገራዊ እና አካታች ምክክር የሚፈልጉ ጉዳዮች አሉ፤ ይሄንን በትውልድ መካከል አንዴ የሚገኝ ዕድል ሳናባክን፤ እያቃናንና እየደገፍን፣ ለኢትዮጵያ ነባር ችግሮች መፍትሔ አዋላጅ እንዲሆን፣ ሁላችንም የድርሻችንን ልንወጣ ይገባናል፤ ዕድሎችን በሰበብ አስባቡ እያባከንን፣ ራሳችንን በችግር አዙሪት የማክረም አካሄድ ማብቃት አለበት። የሽግግር ፍትሕ ሂደትን በሚመለከት ኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ የታሪክ አጋጣሚዎች በደል፣ ግፍ እና መሠረታዊ የመብት ጥሰቶች ተከሥተዋል የቁርሾ እና የቂም በቀል አዙሪት፣ የተበዳይነት እና የብሶት ትርክት በሀገራችን ዋነኛው የፖለቲካ ማጠንጠኛ የሆነበት አንዱ ምክንያትም ይሄው ነው፤ ይሄንን የበዳይ ተበዳይ አዙሪት ለመስበር የሽግግር ፍትሕ አንዱ ተመራጭ ስልት ነው፤ ስለዚህም የሽግግር ፍትሕ ሂደት የሚመራበት የፖሊሲ ማሕቀፍ ጸድቋል፤ የፖሊሲው ዓላማ የሽግግር ፍትሕ ሂደት የሚመራበት እና የሚተገበርበትን ሥርዓት በመዘርጋት ዘላቂ ሰላምን፣ ዕርቅን፣ የሕግ የበላይነትን፣ ፍትሕን እና ዴሞክራሲን ማረጋገጥ ነው፤ በየክልሎች የሚታዩ ታጣቂዎችን በሚመለከት በሀገራችን ከመንግሥት ውጭ የሚኖር የታጠቀን ኃይል ሕገ መንግሥታችን አይፈቅድም፤ የመንግሥትም አንዱ መብት በብቸኝነት ኃይልን መጠቀም ነው፤ ነገር ግን በሀገራችን በወረስነው የፖለቲካ ስብራት የተነሣ የታጠቁ ኃይሎች ተፈጥረዋል፤ የፖለቲካ ጥያቄዎቻቸውንም በሀገራዊ ምክክር ሂደት በመሳተፍ መፍታት ይችላሉ፤ ለዚህ የሚሆን የተሐድሶ ኮሚሽን ተቋቁሟል፤ ዓላማውም መሣሪያ ማስፈታት፣ የትጥቅ ቡድኖችን ሰላማዊ ማድረግና ከማኅበረሰቡ ጋር መቀላቀል ናቸው፤ ይሄንን የተሐድሶ ሥራ በማሳካት ፖለቲካችን ከግንባር ወደ ጠረጴዛ፣ ከጫካ ወደ አዳራሽ እንዲመለስ ማድረግ አለብን፤ የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት አፈጻጸምን በተመለከተ ፦ የፕሪቶሪያው ስምምነት ጦርነትን በፖለቲካዊ መፍትሔ የመቋጨት ባህል አምጥቷል፤ ስምምነቱም ለትውልድ የአሸናፊ ተሸናፊ ትርክትን ከቂም ጋር ላለማውረስ የተደረገ በሳልና ቆራጥ ውሳኔ ነው፤ በአማራ፣ በአፋርና በትግራይ ክልሎች የመልሶ ግንባታ እና የመልሶ ማቋቋም ሥራዎች ተጀምረዋል፤ ሰብአዊ ድጋፍም ያለመሰናከል ወደ ትግራይ መድረስ የሚችልበት ዐውድ ተፈጥሯል፤ በተለይ በስምምነቱ መሠረት የሕወሐት ታጣቂዎች ትጥቅ መፍታት አለባቸው፤ የማንነት እና የአስተዳደር ወሰን ጥያቄ ያለባቸውን አካባቢዎች ጉዳይ እልባት ለመስጠት እንዲቻል የተቀመጠው አቅጣጫ ተግባራዊ መደረግ አለበት፤ በጦርነቱ የተፈናቀሉትን ለመመለስና ለማቋቋም የተጀመረው ሥራ እልባት ማግኘት አለበት፤ የሰላም የትርፍ ድርሻው ታላቅ በመሆኑ መንግሥት ከሚጠበቅበትም አልፎ ቁስልን ለመሻር የሚያስችል ሥራ እየሠራ ነው፤
የሚኒስትሮች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው 31ኛ መደበኛ ስብሰባው ያሳለፋቸው ውሳኔዎች ፦
Apr 25, 2024 118
የወጪ ንግድ የቀረጥ ማበረታቻ ሥርዓት አዋጅን ለማሻሻል የቀረበው ረቂቅ አዋጅ በተመለከተ ለኢንደስትሪ ልማትና ኢንቨስትመንት የሚያስፈልገውን የውጭ ምንዛሪ ግኝት ለማሳደግ፤ በወጪ ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች በማበረታታት ረገድ የታዩ ውስንነቶችን ለመቅረፍ እና የዘርፉን ተዋንያን የሚያበረታታ ሥርዓት በመዘርጋት ተወዳዳሪነት ማላቅ ይቻል ዘንድ ረቂቅ ማሻሻያ አዋጅ ተዘጋጅቶ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ ተደርጓል። የፌዴራል ህብረት ስራ ኮሚሽን ለሚሰጣቸው አገልግሎቶች የሚያስከፍለውን የአገልግሎት ክፍያ ለመወሰን የቀረበ ረቂቅ ደንብን በተመለከተ፦ ኮሚሽኑ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ማስፋት፤ የአገልግሎቶቹን የጥራት ደረጃ ማሻሻል፣ ብሎም የተጠቃሚውን ማህበረሰብ አቅም ባገናዘበ መልኩ አገልግሎት ለመስጠት ያወጣውን ወጪ በከፊል መሸፈን የሚያስችል ስርዓት መዘርጋት በማስፈለጉ ረቂቅ ደንቡ ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡ የጤና ፖሊሲን በተመለከተ በስራ ላይ ያለው የጤና ፖሊሲ ላለፉት ሶስት አስርት ዓመታት ማሻሻያ ሳይደረግበት ቆይቷል፤ ፖሊሲው በጸደቀበት ወቅት ከነበረው ጠቅላላ የህዝብ ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ በመጨመሩ፤ እየተከሰቱ ያሉ ተላላፊና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች መበራከት፤ በሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ደረጃ በጤና ዙሪያ የሚከሰቱ ለውጦች፤ ዘርፉ ጥራት እና ፍትሀዊነት ያለው አገልግሎት ከመስጠት አኳያ ችግሮች የሚስተዋሉበት በመሆኑ፤ እንዲሁም ከሀገራችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት ጋር የሚጣጣም የጤና ፖሊሲ እንዲኖረን አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ረቂቅ ፖሊሲው ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡ በግብርና እና ገጠር ልማት ፖሊሲን በተመለከተ በስራ ላይ የነበረው የግብርና ፖሊሲ ከአዳጊ የምርትና ምርታማነት ፍላጎት ጋር አብሮ መጓዝ የቻለ ባለመሆኑ፤ ለግብርናው ዘርፍ እድገት ማነቆ የሆኑ አሰራሮችን መለወጥ አስፈላጊ በመሆኑ እንዲሁም ሀገራችን ከምትከተለው ብዝሀ ዘርፍ የኢኮኖሚ ስርአት ጋር የሚጣጣም ፖሊሲ ማስፈለጉ ታምኖበታል፤ ስለሆነም የግብርና ዘርፍን ከሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች ጋር የበለጠ የሚያስተሳስር፣ የተፈጥሮ ሃብትን መጠበቅና በዘላቂነት መጠቀም የሚያስችል፤ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እንዲሁም በገጠር መዋቅራዊ ሽግግር ለማምጣት የሚያግዝ ረቂቅ ፖሊሲ ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡
ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች አጀንዳ የማሰባሰብ ተግባር ይጀምራል 
Apr 25, 2024 127
ሀዋሳ፣ሚያዚያ 17/2016 (ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን የተሳታፊዎች መረጣ ባካሄደባቸው ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች አጀንዳ የማሰባሰብ ተግባር እንደሚጀምር የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ አስታወቁ። ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ እንዳሉት ኮሚሽኑ እስካሁን ባለው ሂደት መሠረታዊና የህዝብ ተሳትፎ ባማከለ መልኩ የተሳታፊዎች ልየታና መረጣ በ10 ክልሎችና በሁለቱ ከተማ መስተዳድሮች አገባዷል። በነዚህ አካባቢዎች ያገኛቸውን ልምድ በመጠቀም በአማራና በትግራይ ክልሎች የሀገራዊ ምክክር ተሳታፊዎች ልየታና መረጣ ቀሪ ስራዎች እንደሚከናወኑም አመልክተዋል። በአሁኑ ወቅት የተሳታፊዎች መረጣ ባካሄደባቸው ክልሎችና ሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች ውሰጥ ሰሞኑን አጀንዳ የማሰባሰብ ተግባር እንደሚጀምር ጠቁመዋል። "ለዚህም በየወረዳው የተመረጡ ተወካዮች ወደ ክልላቸው ይመጡና በክልሉ ከሚገኙ 20 ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን የክልላቸውን፣የአካባቢያቸውን ሀገራዊ የሚባሉ አጀንዳዎች ይሰጣሉ "ብለዋል።   ሴቶች፣ አካል ጉዳተኞች፣ የንግዱ ማህበረሰብና መምህራንን ጨምሮ የሁሉም ህብረተሰብ ተወካዮች ለየብቻቸው ከተወያዩ በኋላ በጋራ ያመጡትን አጀንዳ አደራጅተው ወደ ኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን እንደሚልኩ አስረድተዋል። "እነዚህ የተላኩ አጀንዳዎች በሙሉ በሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ታዛቢዎች ባሉበት ግልፅ በሆነ መስፈርት ከተመረጡ በኋላ የቅድሚያ ቅድሚያ የሚሰጣቸው አጀንዳዎች ከተለዩ በኋላ ሀገራዊ ምክክር ይካሄዳል" ብለዋል። ይህንን ለማድረግ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን የቀረው ጊዜ 10 ወር መሆኑን ፕሮፌሰር መስፍን አስታውቀዋል። "በነዚህ ጊዜያት ውስጥ የጎላ እንቅፋት እስካላጋጠመው ድረስ ቢያንስ የሀገራዊ ምክክር ጉባዔውን አስጀምሮና የተወሰኑ አጀንዳዎችን ወደ ማግባባት በማምጣት ማጠናቀቅ እንደሚችል ሙሉ እምነት አለን" ሲሉ ዋና ኮሚሽነሩ አረጋግጠዋል። "ኮሚሽኑ የህዝብ ወገንተኛ መሆኑን በስራችን ለማሳየት እየተጋን እንገኛለን" ሲሉም ተናግረዋል። የሀገራችን ህዝቦች ለብዙ ሺህ ዘመናት ተዋደው፣ተጋብተው፣ተጋምደውና ተስማምተው የኖሩ በመሆናቸው በሀገራዊ ምክክሩ መግባባት ላይ መድረስ እንደማያዳግታቸው ያላቸውን እምነት አስታውቀዋል። በሀገራዊ ምክክሩ የኦሮሚያ ክልል የተሳታፊዎች መረጣና ልየታ ማጠቃለያ መርሀ ግብር በሻሸመኔ ከተማ መካሄዱን ይታወሳል።    
ሙስናና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል ከመንግስት ባለፈ የሁሉም ዜጎችና ተቋማት ርብርብ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት 
Apr 25, 2024 81
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 17/2016 (ኢዜአ)፦ሙስናና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል ከመንግስት ባለፈ የሁሉም ዜጎችና ተቋማት ርብርብ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የፌደራል ሥነ ምግባርና ፀረ- ሙስና ኮሚሽን ገለጸ፡፡ ኢትዮጵያ ሙስናና ብልሹ አሰራርን ለመከላከል አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ የጸረ ሙስና ስምምነቶችን በመቀበል እና ሀገራዊ የህግ ማዕቀፎችን በማውጣት ለተግባራዊነቱ ጥረት እያደረገች ትገኛለች። በተለይም ከለውጡ በኋላ የፌደራል ሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በአዋጅ ቁጥር 1236/2013 እንደገና እንዲቋቋም ተደርጓል። በተጨማሪም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እንደ ሀገር ስር የሰደደውን ሌብነት ለመከላከል ሰባት አባላት ያሉት ብሔራዊ የፀረ ሙስና ኮሚቴ እንዲቋቋም ማድረጋቸው ይታወቃል። የተቋቋመው ብሔራዊ የፀረ ሙስና ኮሚቴ የሙስና ወንጀል ጥቆማዎችን በመቀበል እንደ ሀገር ከፍተኛ ጉዳት ሊያደርስ የሚችል የህዝብና መንግስት ሀብት ከምዝበራ ማዳን እንደተቻለ በሪፖርቱ አረጋግጧል። በፌደራል ሥነ ምግባርና ጸረ ሙስና ኮሚሽን አስቸኳይ የሙስና መከላከል ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ገዛኸኝ ጋሻው ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኮሚሽኑ የሥነ ምግባር አቅም ግንባታ፣ የሙስና ቅድመ መከላከል እና ህግ ማስከበር ስራዎችን እያከናወነ ነው። ከፌዴራል፣ ከክልሎችና ከሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች የፀረ ሙስና ኮሚሽኖች ጋር በመቀናጀት ለተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የአቅም ግንባታ ሥልጠና እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። የኃይማኖት ተቋማት፣ ሲቪክ ማህበራትና የትምህርት ተቋማትን አስተባብሮ የሥነ ምግባር ትምህርት በመስጠት የህብረተሰቡን ሙስናና ብልሹ አሰራር የማጋለጥ ባህል ማሳደግ ተችሏል ብለዋል። ኮሚሽኑ ጥናት በማካሄድና የሃብት ምዝገባ በማከናወን ሙስናን ቀድሞ ከመከላከል ባለፈ፤ በበጀት ዓመቱ ዘጠኝ ወራት በዲጂታል እና በተለያዩ አማራጮች 65 የሙስና ወንጀል ጥቆማዎችን በመቀበል ለፍትህ አካላት ቀርቦ ምርመራ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም እንደ ሀገር 373 የሙስና ቅድመ መከላከል ሥራዎች በማከናወን ከአንድ ነጥብ 384 ቢሊዬን ብር በላይ የህዝብና መንግስት ሃብት እንዲሁም ከ25 ሚሊዬን ካሬ ሜትር በላይ የሆነ የከተማ እና ገጠር መሬት ከምዝበራ ማዳን መቻሉን አስታወሰዋል። በ25 ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች እና ተጠሪ ተቋማት የሙስና ስጋት ያለባቸው ዘርፎችን አሰራር በማጥናት በውጤቱ መሰረት የማስተካከያ እርምጃ እንዲወስዱ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ኮሚሽኑ በሀብት ምዝገባ፣ በእድሳትና አገልግሎት በማቋረጥ ግልጽነትና ተጠያቂነትን ለማስፈን እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም መሰረት እስካሁን የዘጠኝ ሺህ 992 የፌደራል የሥራ ኃላፊዎችና ቡድን መሪዎች ሀብት ምዝገባ ማከናወኑን ተናግረዋል። መንግስት ሙስናና ብልሹ አሰራርን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸው ጉዳዩ የሁሉንም ግለሰቦችና ተቋማት ርብርብ የሚፈልግ መሆኑን ነው የገለጹት።        
ሰላምና ልማትን የማጠናከር ስራ በትኩረት ይከናወናል  -ከንቲባ ከድር ጁሃር
Apr 25, 2024 94
ድሬዳዋ ፤ ሚያዝያ 17/2016 (ኢዜአ)፡- የሰላምና የልማት ውጤታማ ተግባራትን የማጠናከር ስራ በትኩረት ይከናወናል ሲሉ የድሬደዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር አስታወቁ። ለድሬዳዋ አስተዳደር የፖሊስ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች የአቅም ግንባታ ስልጠና እየተሰጠ ነው። በስልጠናው ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት ከንቲባ ከድር ጁሃር እንደተናገሩት አገራዊ ለውጡን ተከትሎ በአዲስ ለውጥና አደረጃጀት የተገነባው ፖሊስ በአርአያነት የሚጠቀሱ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል። ህዝባዊነቱን አፅንቶ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር ተቀናጅቶ ባከናወናቸው ተግባራት በድሬዳዋ አስተማማኝ ሰላምና ፀጥታ መኖሩን ጠቅሰዋል። ሰላምና ፀጥታው በገጠርና በከተማ የተጀመሩ የልማት ስራዎች ውጤታማ እንዲሆኑ አስችሏል ሲሉም አክለዋል። ስራዎቹን ይበልጥ ለማሳደግ የፖሊስ አመራሮችን አቅም የመገንባት ስራም በትኩረት ይተገበራል ብለዋል።   የድሬዳዋ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ኮሚሽነር አለሙ መግራ በበኩላቸው ፖሊስ በዘመናዊ አሠራርና በቴክኖሎጂ ተደግፎ የነዋሪዎችን ዘላቂ ሰላምና ደህንነት ለማረጋገጥ በቁርጠኝነት እየተጋ መሆኑን ገልጸዋል። “ለውጡን ተከትሎ ባከናወናቸው ተግባራት የተገኙ ፍሬዎች በአገር አቀፍ ደረጃ በተሞክሮነት ተቀምረው እየተስፋፉ ናቸው” ብለዋል። እንደ ኮሚሽነር አለሙ ገለፃ ስራዎቹን በላቀ ደረጃ ለማሳደግ የሚሰጠው ስልጠና በቁርጠኝነት ይተገበራል። ለሁለት ቀናት በሚሰጠው የሙያ ስነምግባርና የመረጃ መር አገልገሎት የአቅም ግንባታ ስልጠና ላይ የአስተዳደሩ የፖሊስ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች ተሳትፈዋል።  
የሚኒስትሮች ምክር ቤት በ31ኛ መደበኛ ስብሰባው የተለያዩ ውሳኔዎችን አሳለፈ
Apr 25, 2024 210
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- የሚኒስትሮች ምክር ቤት በ31ኛ መደበኛ ስብሰባው የተለያዩ ውሳኔዎችን አሳልፏል። 31ኛ መደበኛ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ስብሰባ ውሳኔዎች 1. ምክር ቤቱ በቅድሚያ የተወያየው የወጪ ንግድ የቀረጥ ማበረታቻ ሥርዓት አዋጅን ለማሻሻል የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ ነው፡፡ ለኢንደስትሪ ልማትና ኢንቨስትመንት የሚያስፈልገውን የውጭ ምንዛሪ ግኝት ለማሳደግ፣ በወጪ ንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች በማበረታታት ረገድ የታዩ ውስንነቶችን ለመቅረፍ እና የዘርፉን ተዋንያን የሚያበረታታ ሥርዓት በመዘርጋት ተወዳዳሪነት ማላቅ ይቻል ዘንድ ረቂቅ ማሻሻያ አዋጅ ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም ረቂቅ ማሻሻያ አዋጁ ላይ ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 2. በመቀጠል ምክር ቤቱ የተወያየው የፌዴራል ህብረት ስራ ኮሚሽን ለሚሰጣቸው አገልግሎቶች የሚያስከፍለውን የአገልግሎት ክፍያ ለመወሰን በቀረበ ረቂቅ ደንብ ላይ ነው፡፡ ኮሚሽኑ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ማስፋት፣ የአገልግሎቶቹን የጥራት ደረጃ ማሻሻል፣ ብሎም የተጠቃሚውን ማህበረሰብ አቅም ባገናዘበ መልኩ አገልግሎት ለመስጠት ያወጣውን ወጪ በከፊል መሸፈን የሚያስችል ስርዓት መዘርጋት በማስፈለጉ ረቂቅ ደንቡ ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በረቂቅ ደንቡ ላይ ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል በነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውል በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 3. ሌላው ምክር ቤቱ የተወያየው የጤና ፖሊሲ ላይ ነው፡፡ በስራ ላይ ያለው የጤና ፖሊሲ ላለፉት ሶስት አስርት ዓመታት ማሻሻያ ሳይደረግበት መቆየቱ ይታወቃል፡፡ ፖሊሲው በጸደቀበት ወቅት ከነበረው ጠቅላላ የህዝብ ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ በመጨመሩ፣ እየተከሰቱ ያሉ ተላላፊና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች መበራከት፣ በሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ደረጃ በጤና ዙሪያ የሚከሰቱ ለውጦች፤ ዘርፉ ጥራት እና ፍትሀዊነት ያለው አገልግሎት ከመስጠት አኳያ ችግሮች የሚስተዋሉበት በመሆኑ እንዲሁም ከሀገራችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት ጋር የሚጣጣም የጤና ፖሊሲ እንዲኖረን አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ረቂቅ ፖሊሲው ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በረቂቅ ፖሊሲው ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ግብዓቶችን በማከል ከጸደቀበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውል በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 4. በመጨረሻም ምክር ቤቱ የተወያየው በግብርናና ገጠር ልማት ፖሊሲ ላይ ነው፡፡ በስራ ላይ የነበረው የግብርና ፖሊሲ ከአዳጊ የምርትና ምርታማነት ፍላጎት ጋር አብሮ መጓዝ የቻለ ባለመሆኑ፤ ለግብርናው ዘርፍ እድገት ማነቆ የሆኑ አሰራሮችን መለወጥ አስፈላጊ በመሆኑ እንዲሁም ሀገራችን ከምትከተለው ብዝሀ ዘርፍ የኢኮኖሚ ስርአት ጋር የሚጣጣም ፖሊሲ ማስፈለጉ ታምኖበታል፡፡ ስለሆነም የግብርና ዘርፍን ከሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች ጋር የበለጠ የሚያስተሳስር፣ የተፈጥሮ ሃብትን መጠበቅና በዘላቂነት መጠቀም የሚያስችል፤ የግብርና ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እንዲሁም በገጠር መዋቅራዊ ሽግግር ለማምጣት የሚያግዝ ረቂቅ ፖሊሲ ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በረቂቅ ፖሊሲው ላይ ከተወያየ በኋላ ግብአቶችን በማከል ከጸደቀበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውል በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡
የብሪክስ ጥምረት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ሚና ለማጠናከር ዕድል የሚፈጥር ነው
Apr 25, 2024 85
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 17/2016(ኢዜአ)፡- የብሪክስ ጥምረት በአባል ሀገራቱ የሚገኙ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ሚና በልምድ ልውውጥና በፋይናንስ ለማጠናከር ዕድል እንደሚፈጥር የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ገለጸ። የኢትዮጵያ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ከሩሲያ ከመጡ የብሪክስ ጥምረት የሲቪል ማህበረሰብ ባለሙያዎችና ከተለያዩ የሲቪል ማህበራት ጋር ውይይት እያደረገ ነው። የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ፋሲካው ሞላ በዚሁ ወቅት፥ መንግስት ባለፉት የለውጥ ዓመታት ለሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት ሰፊ ሪፎርም ማድረጉን ገልጸዋል። በዚህም የህግ ማሻሻያ በማድረግ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታና በሁለንተናዊ ሀገራዊ ልማት ውስጥ ጉልህ ሚና እንዲጫወቱ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን አንስተዋል። ኢትዮጵያ የብሪክስ አባል ሀገር መሆኗ ሁሉን አቀፍ ተጠቃሚነቷን ለማረጋገጥ እና የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ለማጠናከር ምቹ አጋጣሚ መሆኑንም ተናግረዋል። ኢትዮጵያ ከሩሲያ እና ከሌሎች አባል ሀገራት በሚኖራት ትስስር የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ሰፊ የልምድ ልውውጥ እንዲያደርጉና ተጨማሪ የፋይናንስ አቅም እንዲኖራቸው ዕድል እንደሚፈጥርም አስረድተዋል። የብሪክስ ጥምረት 10 ሀገራት ያሉት ሲሆን የዓለምን 37 በመቶ ኢኮኖሚ እንዲሁም 45 በመቶ የዓለም ህዝብ ቁጥርን ያቀፈ ግዙፍ የትብብር ማዕቀፍ መሆኑ ይታወቃል። ብራዚል፣ ሩሲያ፣ ህንድ፣ ቻይና፣ እና ደቡብ አፍሪካ የብሪክስ መስራቾች ሲሆኑ፥ ኢትዮጵያ፣ ሳዑዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ ግብፅ እና ኢራን በዚህ ዓመት ጥምረቱን ተቀላቅለዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም