ፖለቲካ
በክልሉ የህዝቡን የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በየደረጃው የሚገኙ የምክር ቤት አባላት ሚና ሊጠናከር ይገባል
Jun 14, 2025 52
ጋምቤላ፤ ሰኔ 7/2017 (ኢዜአ)፡-በጋምቤላ ክልል የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና እየተከናወኑ ላሉ ስራዎች ስኬታማነት በየደረጃው የሚገኙ የምክር ቤት አባላት ሚና ሊጠናከር እንደሚገባ የክልሉ ምክር ቤት አፈ- ጉባኤ ወይዘሮ መሠረት ማቲዎስ አመለከቱ። ከክልል እስከ ወረዳ የሚገኙ ምክር ቤቶች ዓመታዊ የጋራ የምክክር መድረክ ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተካሄዷል ።   በምክክር መድረኩ ላይ አፈ ጉባኤዋ እንዳሉት የተዋረድ ምክር ቤቶቹ የወከሉትን ህዝብ በልማት፣ በመልካም አስተዳደርና በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ተጠቃሚ ከማድረግ አንፃር ከፍተኛ ኃላፊነት አለባቸው ብለዋል። በየደረጃው የሚገኙ ምክር ቤቶች በቋሚ ኮሚቴዎች አማካኝነት አስፈፃሚ መስሪያ ቤቶች የሚያዘጋጇቸው የልማት ዕቅዶች በአግባቡ መተግበራቸውን በመከታተልና በመቆጣጠር የህዝቡን ተጠቃሚነት ሊያረጋግጡ እንደሚገባ አመልክተዋል። በተለይም የመንግስትን ውስን ሀብት በአግባቡ ጥቅም ላይ በማዋል ከድህነት ፈጥኖ ለመውጣት ለሚደረገው ጥረት ስኬታማነት ከምክር ቤት አባላት የላቀ ሚና ይጠበቃል ብለዋል። ህዝብ ለሚያነሳቸው የሰላም፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ ከመስጠት አንፃር ምክር ቤቶች ከአስፈጻሚ መስሪያ ቤቶች ጋር ያላቸውን ቅንጅታዊ አሰራር ማጠናከር እንዳለባቸውም አሳስበዋል። በህገ መንግስቱ የተደነገጉ የዜጎች ሰብዓዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ሳይሸራረፉ እንዲተገበሩና በውጤቱም ህዝብን ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት መስራት ይጠበቅብናል ሲሉም አፈ-ጉባኤዋ ገልፀዋል። 'የዛሬው የተዋረድ ምክር ቤቶች የጋራ የምክክር መድረክም ልምዶችን በመለዋወጥ የመደጋገፍ ባህላችንን ለማጠናከር ያለመ ነው ብለዋል።   የምክክር መድረኩ አዘጋጅ የጋምቤላ ከተማ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አቶ ኩዊች ዊው በበኩላቸው መድረኩ የተዋረድ ምክር ቤቶቹ የውክልና ተግባራቸውን በመፈፀም ረገድ ያሉ ጠንካራና ደካማ ጎኖችን በመለየት በቀጣይ ውስንነቶችን ለማረም እገዛ እንዳለውም ተናግረዋል። በዚህም የጋምቤላ ከተማ ምክር ቤት በህገ መንግሥቱ የተሰጠውን ስልጣንና ተግባር በአግባቡ ለመወጣት ከክልሉ ምክር ቤትና ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። የተዋረድ ምክር ቤቶች የምክክር መድረክ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።  
መንግስት ያደሩ ችግሮችን በአምስት ማዕቀፍ ለመፍታት ወስኖ እየሰራ ይገኛል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jun 14, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 7/2017(ኢዜአ)፦ መንግስት ያደሩ ችግሮችን በአምስት ማዕቀፍ ለመፍታት በመወሰን እየሰራ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለፁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከመላው ኢትዮጵያ ከተውጣጡ መምህራን ጋር ተወያይተዋል። በውይይቱም ከመምህራን ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም የመምህራንን ጥያቄ ለመመለስ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተው ነገር ግን ጥያቄው በደሞዝ ጭማሪ ብቻ የሚመለስ አለመሆኑን አብራርተዋል። መንግስት ያደሩ ችግሮችን በአምስት ማዕቀፍ ለመፍታት ወስኖ እየሰራ መሆኑን ያብራሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ የመጀመሪያው አካታች ሀገራዊ ምክክር መሆኑንና ይህም በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያው እንደሆነ አስታውሰዋል።   እንዲሁም የሽግግር ፍትህ፣ የታጠቁ አካላትን በተሐድሶ መልሶ ወደ ህብረተሰቡ መቀላቀል(ዲዲአር)፣ የብዝሀ ዘርፍ የኢኮኖሚ ሪፎርም እና የተቋማት ሪፎርም ሌሎች ማዕቀፎች መሆናቸውን አብራርተዋል። በሌላ በኩል የትምህርት ዘርፋን በጀት በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሰጡት ምላሽ፣ የአንድ ዩኒቨርሲቲ በጀት ከትምህርት ሚኒስቴር በጀት እንደሚበልጥና የእያንዳንዱ ዩኒቨርሲቲ በጀት ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል። መምህራን ማሰብ ያለባቸው ገበታውን እንዴት እናስፋው የሚለውን ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገበታ ለማስፋት ምርታማነት ላይ በጋራ መስራት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። ተቋማትን በማዘመን የመምህራንን ጥያቄ ለመመለስ ይሰራልም ነው ያሉት።   የትምህርት ለትውልድ ንቅናቄ፣ የጋራ ትርክት ግንባታ፣ ምርታማነት፣ የገጠር ኮሪደር እና የትምህርት ጥራት ላይ በጋራ መረባረብ እንደሚያስፈልግ አውስተዋል። ችግሮችን ለመፍታት የተቀመጡ አምስቱ ማዕቀፎችም አድራሽ እንጂ ግብ አይደሉም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለስኬቱ ሁሉም እንዲረባረብ ጥሪ አቅርበዋል።
መንግስት በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን በላቀ ቁርጠኝነት እየሰራ ነው - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jun 13, 2025 93
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ መንግስት በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን በላቀ ቁርጠኝነት እየሰራ እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከመላው ኢትዮጵያ ከተውጣጡ መምህራን ጋር ውይይት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በውይይቱ መንግስት በኢትዮጵያ ሰላምን ለማስፈን እያከናወናቸው ያሉ ስራዎችን አስመልክቶ ማብራሪያ ሰጥተዋል። መንግስት የሰላምን ጉዳይ በተቋም እንስራ በሚል የሰላም ሚኒስቴርን ማቋቋሙን አውስተው ከተቋሙ ባሻገር ከታጠቁ ኃይሎች ጋር ችግሮችን ለመፍታት ያላሰለሰ ጥረት ማድረጉን አመልክተዋል።   ይሁንና መንግስት ለሰላም ያቀረበውን ጥሪ እና የዘረጋውን እጅ ወደ ጎን በመተው ኃይልን እንደ አማራጭ እየተጠቀሙ ያሉ አካላት እንዳሉ ጠቅሰው ከውይይትና ከንግግር ውጪ ሌላ ሰላምን ማምጫ አማራጭ እንደሌለ ሊገነዘቡ ይገባል ብለዋል። ጥሪውን ተቀብለው በሰላማዊ መንገድ እጃቸውን የሰጡ ታጣቂዎችን ከመቀበል ባለፈ በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ ተሳትፎ እንዲኖራቸው በማድረግ ጭምር መንግስት ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት በግልጽ ማሳየቱን አመልክተዋል። ለኢትዮጵያ ሰላም ሲባል ችግሮችን በውይይት መፍታት ለሚፈልግ እና የተሻለ ሀሳብ አለኝ ላለ ማንኛውም አካል መንግስት ሁሌም በሩ ክፍት ነው ሲሉም ገልጸዋል። መንግስት የሰላም ጥሪን ወደ ጎን በመተው ሰውን ማገትና ትምህርት ቤት ማዘጋትን ጨምሮ የኃይል አማራጭን በወሰዱ ኃይሎች ላይ የሕግ ማስከበር እርምጃ እየወሰደ መሆኑን አስታውቀዋል።   የፕሪቶሪያ ንግግር መንግስት ለሰላም ያለውን ጽኑ ቁርጠኝነት በተግባር ያረጋገጠበት ነው ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ሰላም ያስፈጋታል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ይህ እንዲሆን መንግስት በከፍተኛ ትጋት እየሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ሰላም የሚሹ ኃይሎችን የሰላም ግንባታው ሂደት አካል በማድረግ በጋራ እንሰራለን ሲሉም ተናግረዋል።
የኢትዮጵያን በጎ ገጽታ በዓለም አቀፋዊና ቀጣናዊ መድረኮች ለማስተዋወቅ የዜጎችን ንቁ ተሳትፎ ይጠይቃል - የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
Jun 13, 2025 75
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን በጎ ገጽታ በዓለም አቀፋዊና ቀጣናዊ መድረኮች ለማስተዋወቅ ከመደበኛው የመንግሥት ሥራ በተጨማሪ በሀገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ ዜጎች በንቃት መሳተፍ እንዳለባቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ ገለጹ፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና የውጭ ጉዳይ ኢኒስቲትዩት ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ጋር በመተባበር ለወዳጅነት ቡድኖችና ፐብሊክ ዲፕሎማሲ አባላት ያዘጋጁት ስልጠና ተጀምሯል። ከዛሬ ጀምሮ ለሶስት ቀናት በሚቆየው ስልጠና የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ፣ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ፣ የጎረቤት ሀገራትና የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ እንዲሁም ሌሎች የውጭ ግንኙነት ስልቶች ይዳሰሳሉ፡፡   የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርም ሀገራዊ ልማትና ብልጽግናን እውን ለማድረግ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ተለዋዋጭና ኢ-ተገማች በሆነው የዓለም ነባራዊ ሁኔታ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ዘርፈ ብዙ እና የተደራጀ የዲፕሎማሲ ስራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ ተናግረዋል። ለዚህ ደግሞ የዓለም ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ስርዓቱ የሚጠይቀውን የውጭ ግንኙነት ስልት መንደፍና መከተል አስፈላጊ መሆኑን አመልክተው፤ የዓለም አስቻይ ሁኔታዎችን በጥንቃቄ በማየት በአስተውሎት መራመድ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በዚህም የውጭ ንግድና ኢንቨስትመንትን ለመሳብ፣ አጋርነትን ለማጠናከር፣ ገጽታ ለመገንባት፣ የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር ሁሉም አካላት በጋራ መረባረብ አለባቸው ብለዋል። ኢትዮጵያ በአህጉሪቱ በፓን አፍሪካኒዝም መንፈስ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች እንደምትገኝ ገልጸው፤ የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም የሚያስከብሩ ስትራቴጂያዊ አጋሮችን የማብዛት ስራዎችን አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባ ተናግረዋል።   በመርህ ላይ የተመሰረተ ዓለም አቀፋዊ እና ቀጣናዊ አጋርነትን ማሳደግ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ በባለብዙ ወገን መድረኮች የሚተላለፉ ውሳኔዎች የኢትዮጵያን ተደማጭነትና ብሔራዊ ጥቅም የሚያስጠብቁ እንዲሆኑ ማድረግ ይገባል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ፣ የጥንታዊ ስልጣኔ ባለቤት፣ የአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት፣ እንዲሁም የብዝሀ ብሔር መገኛ መሆኗን በፐብሊክ ዲፕሎማሲ ስራችን መግለጽና ገጽታዋን መገንባት አለብን ሲሉም አስገንዝበዋል። ለዚህ ደግሞ መንግስት ከሚሰራው የውጭ ግንኙነት ስራዎች ባሻገር በሀገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡   በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፐብሊክ ዲፕሎማሲ ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ሽብሩ ማሞ በበኩላቸው፤ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ የሀገራችን መልካም ገጽታ መገንባት፣ አጋርነትና ወዳጅነትን ማብዛት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ፐብሊክ ዲፕሎማሲ በመንግሥታት ግንኙነት ብቻ የታጠረውን የሀገራት ግንኙነት በህዝቦች መካከል እንዲዳብር ያስቻለ ነው ብለዋል፡፡ በተለይም የኪነ ጥበብ ባለሙያዎች፣ የምርምር ተቋማትና የተለያዩ የሙያ ማህበራት የሀገርን ገጽታ በማስተዋወቅ በኩል ሚናቸው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
እየተካሔዱ ያሉ የህዝብ ውይይቶች ዜጎች ለብሔራዊ ጥቅም መከበር የበኩላቸውን እንዲወጡ የሚያግዙ ናቸው
Jun 13, 2025 82
ሚዛን አማን፤ ሰኔ 6/2017(ኢዜአ)፦እየተካሔዱ ያሉ የሕዝብ ውይይቶች ዜጎች ሀገራዊ ነባራዊ ሁኔታን በአግባቡ በመረዳት ለብሔራዊ ጥቅም መከበር የበኩላቸውን እንዲወጡ እንደሚያግዙ ኢዜአ ያነጋገራቸው የሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ። መንግስት በዞን፣ በክልልና በከተሞች ደረጃ ከተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎች ተወካዮች ጋር በወቅታዊ ጉዳይ ላይ ተከታታይ ውይይት እያደረገ ይገኛል። ሰሞኑንም ይኽው ውይይት ቀጥሎ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ(ዶ/ር) ከተለያዩ የአገሪቷ አካባቢዎች ከተውጣጡ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ውይይት እያደረጉ ነው። ኢዜአ ያነጋገራቸው የሚዛን ቴፒ ዩኒቨርሲቲ ምሁራንም መንግስት በወቅታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ከዜጎች ጋር እያደረገ ያለው ውይይት ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መጠናከር ትልቅ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የአስተዳደርና ልማት ጥናት ትምህርት ክፍል መምህር ዋሲሁን በዛብህ እንዳሉት ዜጎች ሀገራዊ ነባራዊ ሁኔታን በአግባቡ በመረዳት ለብሔራዊ ጥቅም መከበር የበኩላቸውን እንዲወጡ ተከታታይ ውይይቶች አስፈላጊ ናቸው። ከዚህም ባለፈ እየተደረጉ ያሉ ተከታታይ ውይይቶች የፖሊሲ አቅጣጫዎችን ለዜጎች ለማስገንዘብና አገራዊ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ የጋራ ርብርብ እንዲደረግ ያግዛል ብለዋል። የሀገር ግንባታ የሁሉንም የነቃ ተሳትፎ ይጠይቃል ያሉት መምህር ዋሲሁን ለተግባራዊነቱም መሰል ውይይቶች በሀገራዊ ጉዳይ የጋራ አረዳድ በመያዝ የዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንዲዳብር እንደሚያግዝ አመልክተዋል። በዩኒቨርሲቲው የፖለቲካ ሳይንስ መምህር ቢመርቅ በሪሁን በበኩላቸው እየተካሄዱ ያሉ ውይይቶች ልማትን ለማፋጠንና የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታን ለማጠናከር ያግዛሉ ብለዋል። መንግሥትም ከዜጎች የሚነሱ ጥያቄዎችን በቅርበት ተረድቶ እንደ አስፈላጊነቱ ምላሽ እንዲሰጣቸው ትልቅ እድል ይፈጥራል ሲሉም ገልጸዋል። በተጨማሪም ውይይቶቹ መንግስት ብሔራዊ ጥቅሞችን ለማስከበር የሚያደርገውን ጥረት ለማሳካት ማኅበረሰቡ ነባራዊ ሁኔታዎችን ተገንዝቦ የበኩሉን ድርሻ እንዲያጠናክር የሚያደርግ እንደሆነም አመልክተዋል። በመንግሥትና ሕዝብ መካከል ግልጸኝነትን ለመፍጠር የሚደረጉ መሰል የውይይቶች ለዴሞክራሲ ግንባታ ትልቅ ትርጉም አላቸው ያሉት ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የታሪክና ቅርስ አስተዳደር ትምህርት ክፍል መምህር አለማየሁ አብርሃም ናቸው። በተለይም መንግስት ከምሁራን ጋር የሚያደርገውን ውይይት በማጠናከር ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ ሀሳቦችን የሚያገኝበት መሆኑንም ተናግረዋል።  
ተለዋዋጭ በሆነው የዓለም ነባራዊ ሁኔታ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ዘርፈ ብዙ የዲፕሎማሲ ስራዎችን ማጠናከር ይገባል- አምባሳደር ሃደራ አበራ
Jun 13, 2025 108
አዲስ አበባ፤ሰኔ 6/2017 (ኢዜአ)፦ተለዋዋጭና ኢ-ተገማች በሆነው የዓለም ነባራዊ ሁኔታ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ዘርፈ ብዙ እና የተደራጁ የዲፕሎማሲ ስራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሃደራ አበራ ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና የውጭ ጉዳይ ኢኒስቲትዩት ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ጋር በመተባበር ለወዳጅነት ቡድኖችና ፐብሊክ ዲፕሎማሲ አባላት ያዘጋጀው ስልጠና ተጀምሯል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሃደራ አበራ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርም ሀገራዊ ልማትና ብልጽግናን እውን ለማድረግ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የውጭ ንግድና ኢንቨስትመንትን ለመሳብ፣ አጋርነትን ለማጠናከር፣ገጽታ ለመገንባት፣ የዜጎችን ጥቅም ለማስከበር እና የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር ሁሉም አካላት በጋራ መረባረብ አለባቸው ብለዋል። ተለዋዋጭና ኢ-ተገማች በሆነው የዓለም ነባራዊ ሁኔታ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ዘርፈ ብዙ እና የተደራጀ የዲፕሎማሲ ስራ ማጠናከር እንደሚገባ ተናግረዋል። ለዚህ ደግሞ የዓለም ፖለቲካዊ፣ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ስርዓቱ የሚጠይቀውን የውጭ ግንኙነት ስልት መንደፍና መከተል፤የዓለም አስቻይ ሁኔታዎችን በጥንቃቄ በማየት በአስተውሎት መራመድ እንደሚገባ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ በአህጉሪቱ በፓን አፍሪካኒዝም መንፈስ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን የመሪነት ሚናዋን እየተወጣች መሆኑን ገልጸው፤የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም የሚያስከብሩ ስትራቴጂያዊ አጋሮች የማብዛት ስራዎችን አጠናክሮ መቀጠል ይገባል ብለዋል። ኢትዮጵያ በባለብዙ ወገን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ብሔራዊ ጥቅሟን ማስጠበቅ የሚያስችሉ የነቃ ተሳትፎ ማድረግ እንደሚገባ ገልጸው፣ በመርህ ላይ የተመሰረተ ዓለም አቀፋዊ እና ቀጣናዊ አጋርነትን ማሳድግ ወሳኝ መሆኑን አሳስበዋል። ኢትዮጵያ የሰው ዘር መገኛ፣ የጥንታዊ ስልጣኔ ባለቤት፣የአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት፣ እንዲሁም የብዝሀ ብሔር መገኛ መሆኗን በፐብሊክ ዲፕሎማሲ ስራችን መግለጽና ገጽታዋን መገንባት ይጠበቅብናል ብለዋል። ለዚህ ደግሞ መንግስት ከሚሰራው የውጭ ግንኙነት ስራ ባሻገር በሀገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተናግረዋል።
ፊንላንድ በተለያየ መስክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን አጋርነት ታጠናክራለች - የፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኤሊና ቫልቶነን
Jun 12, 2025 160
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፦ፊንላንድ በተለያየ መስክ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን አጋርነት እንደምታጠናክር የፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኤሊና ቫልቶነን ተናገሩ። ፊንላንድ ለስምንት ተከታታይ ዓመታት በዓለም ቁጥር አንድ የደስተኞች አገር በመባል በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ተሰይማለች። ይህን መነሻ በማድረግ በሀገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋባዥነት የአፍሪካ ጋዜጠኞች በቅርቡ በፊንላንድ ጉብኝት አካሂደዋል። በዚህ ወቅት የፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኤሊና ቫልቶነን ከኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ጋር ባደረጉት ቃለ-ምልልስ ፊንላንድና ኢትዮጵያ ጠንካራ ግንኙነት ያላቸው አገራት ናቸው። ሀገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዘርፈ-ብዙ ግንኙነት ማጠናከር እንደምትፈልግ የገለጹት ሚኒስትሯ በተለይም በልማት፣ በንግድና ኢንቨስትመንት መስኮች የበለጠ ትኩረት እንደሚደረግ ጠቁመዋል። የኢትዮጵያና የፊንላንድ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ከተመሰረተ 66 ዓመታትን አስቆጥሯል። ሁለቱ ሀገራት ለረጅም ዓመታት የቆየ በጋራ ጥቅምና መተማመን ላይ የተመሰረተ የሁለትዮሽ ግንኙነትም አላቸው። የልማት ትብብራቸው በትምህርት፣ በገጠር ልማት፤ በንግድና ኢንቨስትመንት እና በሌሎችም መስኮች ላይ ያተኮረ ነው። ይህ ዘርፈ-ብዙ የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደላቀ ደረጃ ያድጋል የሚል እምነት እንዳላቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ኤሊና ቫልቶነን ተናግረዋል።   በፊንላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የስትራቴጂክ ኮሙኒኬሽንስ ጉዳዮች አምባሳደር አን ላሚላ በበኩላቸው ለኢዜአ እንደገለጹት የሚዲያ ጉብኝቱ ዓላማ ስለ ፊንላንድ ማሳወቅና የስኬት ምስጢሮችን ማካፈል ብቻ ሳይሆን ሀገሪቱ ከአፍሪካ ጋር ያላትን ግንኙነት ማሳደግ ጭምር ነው። ፊንላንድ ከአፍሪካ ሕብረት፤ በተናጥልም ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ጋር ስትራቴጂክ አጋርነት እንዳላት የገለጹት አምባሳደሯ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት ግንኙነትም ጠንካራ መሰረት ያለው መሆኑን አስታውሰዋል። የደስተኛ ህዝቦች መኖሪያ የምትሰኘው ፊንላንድ ግብር ከፋይ የአገሪቱ ዜጎች በታማኝነትና በደስታ ግብር የሚከፍሉባት ሰሜን አውሮፓዊት ሀገር ነች። በትምህርት፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በጾታ እኩልነት፤ እንዲሁም በጤናና ለማህበረሰብ ምቹ ቤተሰብ መፍጠርን ጨምሮ ባከናወነቻቸው ጠንካራ የማህበራዊ ደህንነት ትስስር ስራዎች ዜጎቿ ደስተኞች መሆናቸው ይገለጻል።
አርሜኒያ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ታሪካዊ ወዳጅነት ወደላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ትሰራለች - ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቫሃን ኮስታንያን
Jun 12, 2025 102
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፦ አርሜኒያ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ታሪካዊ ወዳጅነት ወደላቀ ደረጃ ለማሸጋገር እንደምትሰራ የአርሜኒያ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቫሃን ኮስታንያን ገለጹ። የአርሜኒያ ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቫሃን ኮስታንያን እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያና አርሜኒያ ታሪካዊና ጠንካራ የሁለትዮሽ ወዳጅነት አላቸው። በአራተኛው ክፍለ ዘመን የተጀመረው የኢትዮጵያና አርሜኒያ ግንኙነት እያደገና ዘላቂ ወዳጅነት እያስመዘገበ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በአዲስ አበባ የሚታየው የአርሜኒያ ህዝቦች አሻራም የሁለቱን ሀገራት የህዝብ ለህዝብ ጥልቅ ወዳጅነት የሚያሳይ መሆኑን ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የሚገኙት አነስተኛ ቁጥር ያላቸው የአርሜኒያ ማህበረሰብም በአዲስ አበባ በንግድና በዕደ-ጥበብ ሙያ በመሰማራት ከኢትዮጵያዊያን ጋር በጥብቅ ወዳጅነትና አብሮነት እየኖሩ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአዲስ አበባ የአርሜኒያዊያን የስራ ባህል ውርስ የሆኑ ጌጣ ጌጦች፣ ኪነ-ጥበበኞች፣ ነጋዴዎችና የተለያዩ የሙያ ጠበብቶች መኖራቸውን ጠቁመዋል። በአሁኑ ወቅትም በኢትዮጵያና አርሜኒያ መካከል አንዳቸው ለአንዳቸው ቅርብ አጋር የሚሆኑበት ከፍተኛ ዕድል መኖሩን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ አክለዋል። የኢትዮጵያ ጉብኝታቸውም የኢትዮ-አርሜንያን ህዝቦች የባህል፣ የትምህርት፣ ቴክኖሎጂና የጤና መስክ የሁለትዮሽ ግንኙነት ለማጠናከር ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው አብራርተዋል። ለአብነትም በኢትዮ-አርሜኒያን መካከል ያለውን ትብብር ለማጠናከር የሳይንስ፣ የባህልና ትምህርት ስምምነት መፈረሙን አስታውሰዋል። በቀጣይም የጋራ የመንግስታት ኮሚሽን በማቋቋም የፖለቲካና ሌሎች የትብብር መስኮችን ለማጠናከር የሃሳብ ልውውጥ መደረጉን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ ቆይታቸውም ፖለቲካዊ ምክክር፣ ቀጣናዊ፣ አፍሪካዊና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮችን የዳሰሰ መሆኑን አስረድተዋል። በምክክር መድረኩም ኢትዮጵያና አርሜኒያ በተባበሩት መንግስታት ድርጅትና በሌሎች ዓለም አቀፍ ተቋማት አባልነታቸውን በመጠቀም ያላቸውን የነቃ ተሳትፎ ለማጠናከር አጽንኦት እንደተሰጠ አብራርተዋል።  
አዲስ ተሿሚ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አመራሮች ሀገራዊ ተልዕኳቸውን በአግባቡ ሊወጡ ይገባል-ምክር ቤቱ
Jun 12, 2025 143
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፦ አዲስ ተሿሚ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አመራሮች ሀገራዊ ተልዕኳቸውን በአግባቡ ሊወጡ እንደሚገባ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አሳሰበ። ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 36ኛ መደበኛ ስብሰባ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድን ምክትል ሰብሳቢ እና የሥራ አመራር ቦርድ አባላትን ሹመት በሁለት ድምጸ ተዓቅቦ በአብላጫ ድምጽ አጽድቋል።   በዚህም አቶ ተስፋዬ ንዋይን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ እንዲሁም አቶ ተክሊት ይመስል እና ወይዘሮ ነሲም አሊን የሥራ አመራር ቦርድ አባላት አድርጎ ሹሟል። የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ ቤልጅጌ (ዶ/ር) የቀረቡ እጩዎችን በተመለከተ ለምክር ቤቱ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡ ተጠሪ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው ተሿሚዎቹ በህገ መንግስቱ መሰረት የሚደረጉ ምርጫዎችና ህዝበ ውሳኔዎች በፍትሐዊነትና ገለልተኝነት ማስፈጸም የሚችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡   ተሿሚዎች የትምህርት ዝግጅታቸውና ከዚህ በፊት በፍትሕ ዘርፉ የሰሩባቸው የሥራ ልምዶችና የነበራቸው አፈፃፀም ኃላፊነታቸውን በብቃት እንደሚወጡ ማሳያዎች ናቸው ብለዋል፡፡ ቀደም ብሎ ሥራውን በጥራትና በብቃት ማከናወን የሚችሉ መልማይ ኮሚቴዎች ተለይተው ከህዝብ፣ ከሲቪክ ማህበራትና ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጥቆማ ተቀብለው ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ማቅረባቸውን ተናግረዋል፡፡ ከተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራርና አባላት ጋር ምክክር መደረጉን ገልጸው፤ ተሿሚዎቹ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተዓማኒነቱን አስጠብቆ እንዲቀጥል የሚያስችሉና የማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት አባል ያልሆኑ መሆናቸውን አመልክተዋል። ተጠሪ ሚኒስትሩ አክለውም የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ ሆነው የተሾሙት አቶ ተስፋዬ ንዋይ የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት እና የፌደራል ፍርድ ቤቶች ቃል አቀባይ ሆነው ስራቸውን በብቃት ማከናወናቸውን አውስተዋል፡፡ የሥራ አመራር ቦርድ አባል ሆነው የተሾሙት አቶ ተክሊት ይመስል የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት እንዲሁም ወይዘሮ ነሲም አሊ የሀረሪ ክልል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኛ በመሆን ውጤታማ ሥራ ማከናወናቸውን ገልጸዋል፡፡ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በበኩላቸው፤ ተሿሚዎቹ ከዚህ በፊት ያላቸው ልምድ ገለልተኛ ሆነው መሥራት እንደሚችሉ እንደሚያሳይ ተናግረዋል፡፡ የማንኛውም ፖለቲካ ድርጅት አባል አለመሆናቸውና በሙያቸው ምስጉን መሆናቸው ሀገርና ትውልድን የሚያሻግር ሥራ እንደሚሰሩ እምነት እንዲኖረን አድርጓል ነው ያሉት፡፡ ተሿሚዎች በምክር ቤቱ የተሰጣቸውን ሀገራዊ ኃላፊነት በብቃት መወጣት እንዳለባቸውም ገልጸዋል።   የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶ፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሥራ አመራር ቦርድ አባላት ሹመት በውሳኔ ቁጥር 10/2017 በአብላጫ ድምፅ መጽደቁን አስታውቀዋል፡፡ ምክር ቤቱ በስብሰባው የውጭ ሀገር የስራ ስምሪት ረቂቅ አዋጅን ለሰው ሀብት ልማት ሥራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ እንዲሁም የዕፅዋት ጥበቃ እና ኳራንታይን ረቂቅ አዋጅን ለግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለዝርዝር እይታ መርቷል።
ሰራዊቱ የሀገርን ሉዓላዊነት በማስጠበቅ አለኝታነቱን አስመስክሯል
Jun 12, 2025 104
አሶሳ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ):- ሰራዊቱ የሀገርን ሉዓላዊነት በማስጠበቅ አለኝታነቱን አስመስክሯል ሲሉ የመከላከያ ሰራዊት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ኮሎኔል ጌትነት አዳነ ገለጹ። በቴክኖሎጂ የበለጸገና ለሌሎች ሀገራትም ምሳሌ የሚሆን መከላከያ ሰራዊት መገንባቱንም አክለዋል። በምዕራብ ዕዝ የ404ኛ ህዳሴ ኮር 3ኛ ዓመት የምስረታ በዓል "ህዳሴን በህዳሴ" በሚል መሪ ሃሳብ በአሶሳ ከተማ በፓናል ውይይት ተከብሯል። በመድረኩ 404ኛ ህዳሴ ኮር የአካባቢውን ሠላም በማስጠበቅ ረገድ እና በልማት ስራዎች ላይ እያደረገ ያለውን ተሳትፎ በተመለከተ በአሶሳ ዩኒቨርሲቲ መምህራን የመነሻ ጽሁፍ ቀርቧል። በመድረኩ የተገኙት የመከላከያ ሰራዊት የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር ኮሎኔል ጌትነት አዳነ እንደተናገሩት ሰራዊቱ የሀገርን ሉዓላዊነት በማስጠበቅ አለኝታነቱን አስመስክሯል። በቴክኖሎጂ የበለጸገና ለሌሎች ሀገራትም ምሳሌ መሆን የሚችል ሰራዊት እየተገነባ መሆኑንም አንስተዋል። ኮሩ በአካባቢው የነበረው የፀጥታ ችግር እንዲቀረፍ ከከፈለው መስዋዕትነት ባለፈ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ በአስተማማኝ ሁኔታ ግንባታው እንዲከናወን አስተዋጽኦ አድርጓል ብለዋል። ሰራዊቱ ከመደበኛ ተልዕኮው በተጨማሪ በሰብዓዊ ድጋፍ የሀገር አለኝታነቱን እያስመሰከረ መሆኑን ጠቁመው በደም ልገሳ፣ በአካባቢ ጥበቃናና በሌሎች ተግባራት እያደረገ ያለው ተሳትፎ የህዝብ ወገንተኝነቱን ያረጋገጠበት ነው ሲሉም ገልጸዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጌታሁን አብዲሳ በበኩላቸው፤ ሰራዊቱ በሀገሩ የማይደራደር፣ የሀገር ኩራት እና በሰብዓዊ ድጋፎች ረገድ ጠንካራ ተሳትፎ እያደረገ ያለ ሰራዊት ነው ብለዋል። ክልሉ በሙሉ አቅሙ ፊቱን ወደ ልማት ስራዎች እንዲያዞር የምዕራብ ዕዝ ሠላምን በማስጠበቅ አኩሪ ገድል መፈጸሙን ጠቁመዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል ኢብራሂም አዙቤር እና ፍቃዱ አማረ ሰራዊቱ በክልሉ ለተገኘው ሠላም ያበረከተው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰዋል። ህብረተሰቡም ለሰራዊቱ ያለው ክብር ከፍተኛ ነው ያሉት አስተያየት ሰጪዎቹ የሀገርን ሠላምና የህዝቦችን አንድነት ማስጠበቅ ላይ አበርክቶው የጎላ መሆኑን አንስተዋል። በመድረኩ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጌታሁን አብዲሳ፣ የክልሉ ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አስካለች አልቦሮ፣ በብልፅግና ፓርቲ የክልሉ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኢስሃቅ አብዱልቃድር፣ በምዕራብ ዕዝ የ404ኛ ህዳሴ ኮር አዛዥ ኮሎኔል ንጉሴ ለውጤ፣ የሰራዊቱ አመራሮች፣ የክልሉ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የሰራዊት አባላት፣ የተለያዩ የፀጥታ አካላት በተገኙበት በፓናል ውይይት እየተከበረ ይገኛል።
የሲዳማ ክልል ምክር ቤት የአቶ አለማየሁ ጢሞቲዎስን ያለመከሰስ መብት አነሳ
Jun 12, 2025 86
ሀዋሳ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፦ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት የክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ሃላፊን አለማየሁ ጢሞቲዎስን ያለመከሰስ መብት አነሳ። ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው 6ኛ ዙር 4ኛ የስራ ዘመን 2ኛ አስቸኳይ ጉባኤ ነው የምክር ቤት አባሉን ያለመከሰስ መብት ያነሳው። የሲዳማ ክልል ፍትህ ቢሮ ሃላፊ ማቶ ማሩ በሙስና ወንጀል፣ ስልጣንን አለአግባብ በመጠቀም፣ በህገ ወጥ ንግድና መሳሪያ ዝውውርና በአደንዛዥ እጽ ዝውውር ማስፋፋት የተጠረጠሩትን አቶ አለማየሁ ጢሞቲዎስ ያለመከሰስ መብታቸው እንዲነሳ ለምክር ቤቱ ባቀረቡት ማብራሪያ ነው ምክር ቤቱ ተቀብሎ ከተወያየ በኋላ በሙሉ ድምጽ ያጸደቀው። ምክር ቤቱ በተጨማሪም የሲዳማ ብሮድካስት ኮርፖሬሽንን ስያሜ ለመቀየር በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ ተወያይቷል። በዚህም መሰረት የሲዳማ ብሮድካስት ኮርፖሬሽን ስያሜ እንዲቀየር የቀረበው ረቂቅ አዋጅ በምክር ቤት አባላት ተቀባይነት አላገኘም። በዚህም የቀረበው ረቂቅ አዋጅ እንደገና በጥናት ተደግፎ እንዲቀርብ ምክር ቤቱ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል። የምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ምክር ቤቱ በአስቸኳይ ጉባኤው በሁለት አጀንዳዎች ላይ በጥልቀት ተወያይቶ ውሳኔ ማሳለፉን አስታውቀዋል።
በፓርላማ ዲፕሎማሲ ብሔራዊ ጥቅምን በማስጠበቅ ግንኙነትን ያጠናከሩ ስኬታማ ስራዎች ተከናውነዋል
Jun 12, 2025 132
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፦ በፓርላማ ዲፕሎማሲ ባለፉት አራት አመታት የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅ ግንኙነትን ያጠናከሩ ስኬታማ ስራዎች መከናወናቸውን አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ተናገሩ። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ኢትዮጵያ ከሌሎች ሀገሮች ጋር ያላትን ግንኙነት ለማጠናካር ከሚያከናውናቸው ተግባራት መካከል የፓርላማ ዲፕሎማሲ አንዱ ነው። በምክር ቤቱ የውጭ ግንኙነትና ሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባልና የአውሮፓ ህብረት የምዕራብ አውሮፓና የኢትዮጵያ የፓርላማ የወዳጅነት ቡድን ሰብሳቢ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ባለፉት አራት አመታት በፓርላማ ዲፕሎማሲ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከአፍሪካ፣ ከአውሮፓ፣ ከምስራቅ አውሮፓ፣ ከእስያ፣ ላቲን አሜሪካና ሌሎች ሀገሮች ጋር የፓርላማ የወዳጅነት ቡድን መስርቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። በፓርላማ ቡድኖች አማካኝነት ከአለም ሀገራት ጋር በፖለቲካ፣ በምጣኔ ሃብት፣ በማህበራዊና በጸጥታ ዘርፍ ያላትን ግንኙነት የሚያጠናክሩ ውይይቶችና የልምድ ልውውጦች መደረጋቸውንም ተናግረዋል። በዚህም የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅና ዓለም አቀፍ ግንኙነትን በማጠናከር በኩል ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል። በጎረቤት ሀገሮች የፓርላማ ዲፕሎማሲ ቀጠናዊ ትስስርና የጋራ ተጠቃሚነትን የሚያጠናክሩ በርካታ ስራዎች መከናወናቸውንም አንስተዋል። እንደ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ገለጻ ኢትዮጵያ ያራመደቻቸው አቋሞች፣ የተካሄዱ ውይይቶችና የተደረጉ ግንኙነቶች ወዳጅነትን የሚያሳድጉ ናቸው። በኢትዮጵያ ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ፣ በቀጣናዊ ጉዳዮች ያላትን ሚና እንዲሁም የተጀመረውን ሪፎርምና የተገኙ ውጤቶችን በማስረዳት በኩል ትልቅ የዲፕሎማሲ ስራ መከናወኑንም ገልጸዋል። ኢትዮጵያ የአየር ንብርት ለውጥን ለመቋቋም በአረንጓዴ አሻራ ያስመዘገበችውን ስኬትና እያከናወነች ያለውን ተግባር በውይይቶችና በዓለም አቀፍ መድረኮች ልምዷን ማካፈሏን አስታውቀዋል። በምግብ እራስን ለመቻል በግብርና እና የሌማት ትሩፋት እንዲሁም ዘመናዊ ከተሞችን ለመገንባት በኮሪደር ልማት እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትም ሀገራት ልምድ የወሰዱባቸው ናቸው ብለዋል። ኢትዮጵያ ባለፉት አራት አመታት ስኬቶችን ያስመዘገበችበት እንዲሁም በፈተናዎች ውስጥ ያለፈችበት ጊዜ በመሆኑ ለአቻ የፓርላማ አባላት በማስረዳት የፓርላማ ዲፕሎማሲ ትልቅ ሚና ተጫውቷል ነው ያሉት። የኢትዮጵያ ታላቁ ህዳሴ ግድብ በየትኛውም አካል ላይ ጉዳት እንደማያደርስ፣ ለጎረቤትና ለተፋሰሱ ሀገራት ትልቅ ጠቀሜታ እንዳለው በማስረዳት በኩልም ውጤት መገኘቱን አንስተዋል። በቀጣይ በሰጥቶ መቀበል መርህ ተለዋዋጭ የሆነውን የዓለም አቀፍ ፖለቲካ ከግምት በማስገባት ብሔራዊ ጥቅምን የሚያስጠብቁ ግንኙነቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቁመዋል። የሀገርን ጥቅም ማስከበር የሁሉም ዜጋ ኃላፊነት በመሆኑ የሲቪል ማህበራት፣ መገናኛ ብዙሃንና ግለሰቦች በአንድነት መስራት እንዳለባቸውም አምባሳደሩ አስረድተዋል።
አሰባሳቢ ትርክቶችን በማስረፅና የጋራ በሆኑ ማንነቶች ግንባታ ላይ የተጀመሩ ስራዎችን አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል
Jun 12, 2025 79
ሰመራ፤ ሰኔ 5/2017(ኢዜአ)፦ የሚዲያና የኮሙኒኬሸን ባለሙያዎች አሰባሳቢ ትርክቶችን በማስረፅና የጋራ በሆኑ ማንነቶች ግንባታ ላይ የተጀመሩ ስራዎችን አጠናክረው ማስቀጠል እንደሚገባቸው በብልፅግና ፓርቲ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ(ዶ/ር) አስታወቁ። ''የድህረ እውነት ዘመንን በእውቀትና በእውነት” በሚል መሪ ሐሳብ ለአፋር ክልል አመራሮችና የሚዲያና የኮሙኒኬሸን ባለሙያዎች በሰመራ ከተማ ስልጠና እየተሰጠ ነው። በብልፅግና ፓርቲ የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት ባለፉት ሰባት የለውጥ አመታት አሰባሳቢ ትርክቶችን በማስረፅና የጋራ በሆኑ ማንነቶች ላይ ትኩረት በማድረግ ሲሰራ ቆይቷል። በዚህም ህብረ ብሄራዊ ለሆነው የአንድነት ጉዞ የጸና መሰረት ማኖር መቻሉን ተናግረዋል። በድህረ እውነት ዘመን የጋራ ወንድማማችነትንና እህትማማችነትን በሚያሳድጉ ጉዳዮች ላይ ማተኮር እንደሚገባ ጠቁመው በዚህ በኩል የሚዲያና የኮሙኒኬሸን ባለሙያዎች በለውጡ አመታት የተገኙ ውጤቶችን አጠናክረው ማስቀጠል እንደሚገባም አሳስበዋል። በመድረኩ የተገኙት በብልፅግና ፓርቲ የአፋር ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ሀላፊ መሐመድ ሁሴን በበኩላቸው ባለፉት ሰባት ዓመታት ህብረ ብሄራዊ አንድነት መጠናከሩን ገልጸዋል። የሚዲያና የኮሙኒኬሸን ባለሙያዎች የጋራ ትርክትን ማሰረፅ ላይ በትኩረት ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ስልጠናው ለተከታታይ ሶስት ቀናት እንደሚቆይ ተመላክቷል።
ኢትዮጵያ እና ቻይና የባለብዙ ወገን ትብብራቸውን ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ
Jun 11, 2025 97
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 4/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና ቻይና በባለብዙ ወገን የትብብር አማራጭ ግንኙነታቸውን የበለጠ ለማጎልበት እንደሚፈልጉ አስታወቁ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ(ዶ/ር) ከቻይና አፍሪካ መድረክ(ፎካክ) የአፈጻጸም ክትትል የሚኒስትሮች ስብሰባ ጎን ለጎን ከቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ ጋር ተወያይተዋል። ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ(ዶ/ር) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለቻይናው ፕሬዝዳንት ሺ ጂን ፒንግ ያቀረቡትን ሰላምታ በቻይናው አቻቸው በኩል አድርሰዋል። የኢትዮጵያና ቻይና በሁኔታዎች የማይለዋወጥ ስትራቴጂያዊ አጋርነት በማጠናከር እና በ2024 የቤጂንግ የመሪዎች ጉባኤ ፕሬዝዳንት ሺ ጂን ፒንግ ያቀረቧቸውን የፎካክ 10 የአጋርነት ተግባራትን በመተግበር ረገድ ትልቅ ለውጥ መመዝገቡን ሚኒስትሩ ገልጸዋል።   የሁለቱ ሀገራት አጋርነት በደቡብ ደቡብ ትብብር፣ በብሪክስ እና በተመድ እንዲሁም በሌሎች መስኮች ያለው ትብብር ጥሩ ማሳያ እየሆነ መምጣቱን አመልክተዋል። በቻይና፣ አፍሪካ እና የተባበሩት መንግሥታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት(ዩኒዶ) የሦስትዮሽ አጋርነት በአዲስ አበባ የተከፈተው የኢንዱስትሪ የልህቀት ማዕከል ለአፍሪካ የኢንዱስትሪ ዝመና ከፍተኛ ሚና የሚጫወት እና በአፍሪካ ቻይና ግንኙነት ላይ ጉልህ አሻራ የሚያሳርፍ መሆኑንም ነው ሚኒስትሩ ያነሱት። የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ በበኩላቸው ከአሁን በፊት የሁለቱ ሀገራት መሪዎች የጋራ መግባባት የደረሱባቸውን መስኮች ወደ ተግባር መለወጥ እንደሚገባ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ እና ቻይና የደቡብ ደቡብ ትብብር እና የብሪክስ ወሳኝ አባል መሆናቸውን አመልክተዋል። ዋንግ ዪ ቻይና ኢትዮጵያን ሁነኛ አጋር እና ወዳጅ አድርጋ እንደምትመለከታት በመግለጽ የተሻለ ልማት እንዲመዘገብ አጋርነቱን የበለጠ ማጠናከር እንደሚገባ መግለጻቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
የኦዲት ባለድርሻ አካላት ፎረም ተቋማት በሀላፊነት ተልዕኳቸውን እንዲፈጽሙ የሚያግዝ በመሆኑ ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jun 11, 2025 80
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 4/2017(ኢዜአ)፦ የኦዲት ባለድርሻ አካላት ፎረም ተቋማት በባለቤትነትና በሃላፊነት ተልዕኳቸውን እንዲፈጽሙ የሚያግዝ በመሆኑ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሺመቤት ደምሴ(ዶ/ር) ገለጹ። ቋሚ ኮሚቴ የኦዲት ባለድርሻ አካላት ፎረም የ2017 በጀት አመት አፈፃፀም ላይ ውይይት አካሒዷል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ የሺመቤት ደምሴ(ዶ/ር) የኦዲት ባለድርሻ አካላት ፎረም እቅድ አፈጻጸም ማጠቃለያ ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ ከኦዲት ግኝት ጋር ተያይዞ አስተያየት ከተሰጣቸው ተቋማት ውስጥ ለሶስት ተቋማት የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ እንዲሁም ኃላፊዎች የገንዘብ ቅጣት እንዲጣልባቸው መደረጉን ተናግረዋል። በተጨማሪም ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትን ጨምሮ ለሰባት የመንግስት ተቋማት የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ እንዲደርሳቸው መደረጉን አንስተው በበጀት ዓመቱ በተከናወኑ የኦዲት ግኝት ተግባራት ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት መቻሉን ተናግረዋል። ይህም የኦዲት ባለድርሻ አካላት ፎረም የተቋማትን አሰራር በመፈተሽ የቁጥጥር ስርዓትን ለማጠናከርና ተጠያቂነትን ለማስፈን አስቻይ ሁኔታ መፍጠሩን ገልጸዋል። የውይይቱ ተሳታፊዎች በበኩላቸው ፎረሙ ተቋማት በኦዲት ግኝት ዙሪያ ያላቸው ግንዛቤ እንዲጨምርና የበጀት አጠቃቀም ስርዓታቸው ጥንቃቄ የታከለበት እንዲሆን አድርጓል ብለዋል። የፍትህ ሚኒስትር ሐና አርያስላሴ የኦዲት የጋራ ፎረሙ የሁሉም ተቋማት የጋራ የትኩረት አቅጣጫ ነው ብለዋል። የጋራ ፎረሙ በቋሚ ኮሚቴው የተገኙ ግኝቶችን በግብዓትነት ለመውሰድና ተጠያቂነትን ለማስፈን ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል ነው ያሉት። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ኢዮብ ተካልኝ(ዶ/ር) በበኩላቸው በቋሚ ኮሚቴው የቀረበው ሪፖርት በበጀት ዓመቱ በዘርፉ በርካታ ተግባራት መከናወናቸውን የሚያሳይ ነው ብለዋል። ይህም በተቋማት መካከል ተናቦ የመስራት ልምድ እንዲዳብርና በኦዲት ግኝት ዙሪያ ትርጉም ያለው ለውጥ ለማምጣት አይነተኛ ሚና አለው ሲሉም ገልጸዋል። የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ጥሩማር አባተ በቋሚ ኮሚቴው የሚሰሩ የክዋኔም ሆነ የፋይናንስ ኦዲት ተግባራት ፕላንና ልማት ሚኒስቴር ለሚያከናውነው የተቋማት አፈጻጸም ግምገማ መሰረት የሚሆን ነው ብለዋል። በተለይም በሀገር አቀፍ ደረጃ ተግባራዊ ለሚደረገው ''አንድ እቅድ አንድ ሪፖርት አንድ እቅድ አንድ በጀት'' የሚለው አሰራር ተግባራዊ እንዲሆን አስቻይ ሁኔታ ይፈጥራል ነው ያሉት። በፌዴራል ስነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን የሙስና መከላከል ጥናት ዴስክ ኃላፊ ደምሴ ስንሻው በበኩላቸው ፎረሙ የኦዲት ግኝትን መነሻ በማድረግ ተጠያቂ እንዲሆኑ ያደረጋቸው ተቋማትና የስራ ሃላፊዎች በሪፖርቱ መካተቱ በኦዲት ግኝትም ሆነ ከመልካም አስተዳደር ጋር ተያይዞ የሚፈጸሙ ወንጀሎች በቀላሉ እንደማይታለፉ የሚያሳይ ነው ብለዋል። የፌዴራል ዋና ኦዲተር ምክትል ዋና ኦዲተር አበራ ታደሰ በበኩላቸው፤ በበጀት ዓመቱ ለሁሉም ባለድርሻ አካላት የኦዲት ሪፖርቱ እንዲደርስ መደረጉን አመልክተው፤ ያካሔደው የክትትልና የቁጥጥር ስራ የሚበረታታ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ ፎረሙ የተቋማት አሰራር ጠንካራና ህጋዊ መስመርን የተከተለ በማድረግ በኩል ጉልህ አስተዋጽኦ እንደሚኖረውም ምክትል ኦዲተሩ አብራርተዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደርና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሺመቤት ደምሴ(ዶ/ር) በሰጡት ማጠቃለያ የኦዲት ባለድርሻ አካላት ፎረም የሚወስደው አስተዳደራዊ እርምጃ አላማው ቅጣት ሳይሆን የአሰራር ማሻሻያን ማምጣት ነው ብለዋል። ይህም ተቋማት በባለቤትነትና በሃላፊነት ተልኳቸውን እንዲፈጽሙ የሚያግዝ በመሆኑ መጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል።
የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ በሚደረገው ጥረት የፖለቲካ ፓርቲዎች ተሳትፎ ሊጎላ ይገባል
Jun 10, 2025 100
አዲስ አበባ፤ሰኔ 3/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ በሚደረገው ጥረት የፖለቲካ ፓርቲዎች ተሳትፎ ሊጎላ እንደሚገባ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዲሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህ ገለጹ። በኢትዮጵያ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ ትኩረት ያደረገ እና የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችን ያሳተፈ ውይይት ተካሂዷል።   አቶ አደም በኢትዮጵያ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ፣እውነታዎችና ኃላፊነቶች ዙሪያ የሚያጠነጥን የውይይት ሰነድ ያቀረቡ ሲሆን ወቅታዊ የሠላም ሁኔታ፣የፖለቲካ ምህዳር እንዲሁም ቀጣናዊ ጉዳዮችን ባቀረቡት ሰነድ ዳስሰዋል። በኢትዮጵያ የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት ተሳትፎን የሚገድቡ ህጎች ላይ ማሻሻያ ከማድረግ ባለፈ ነጻና ገለልተኛ የዲሞክራሲ ተቋማት ለመፍጠር ተግባራዊ እንቅስቃሴዎች ተደርገዋል ብለዋል። አካታች ሀገራዊ ምክክር ሂደት መጀመሩ ትልቅ ዕድል ይዞ የሚመጣ የፖለቲካ ምዕራፍ መሆኑን ገልጸው ከዚህ ቀደምም ከታጠቁ ኃይሎች ጋር የተደረገው የሠላም ሥምምነት ለፖለቲካ ምህዳሩ ዓይነተኛ ሚና እንደሚጫወትም ጠቁመዋል። እንደ አቶ አደም ገለጻ ጽንፍ የረገጡ እሳቤዎች ፣ነጠላ ትርክትና የተዛቡና ሀሰተኛ መረጃዎች የፖለቲካ ምህዳሩ በሚፈለገው ደረጃ እንዳይሰፋ ከሚያደርጉ ጉዳዮች መካከል መሆኑን አመልክተዋል። የፖለቲካ ምህዳሩ ይበልጥ ለማስፋት የጋራ ርብርብ ይጠይቃል ያሉት አቶ አደም ፤ የዲሞክራሲ ተቋማትን ማጠናከር፣ በሀሳብ የበላይነት የሚያምን የሰለጠነ የፖለቲካ ባህል ግንባታን እውን ማድረግ ቀጣይ የትኩረት አቅጫዎች መካከል መሆኑን አመልክተዋል። የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም ማስከበር ጉዳይ የጋራ አጀንዳ በማድረግ በጋራ መግባባት መንፈስ መሥራት እንደሚገባም ተናግረዋል። አካታች ሀገራዊ ምክክሩ ግቡን እንዲመታ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተሳትፎ ጉልህ ሊሆን እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል።   የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ሠለሞን አየለ በበኩላቸው፤ ምክር ቤቱ ለዘላቂ ሠላም መስፈን የበኩሉን ጥረት ሲያደርግ መቆየቱን ጠቅሰዋል። አንድነትን ማጠናከር ለችግሮቻችን ዘላቂ እልባት ለማበጀት ሁነኛ መፍትሄ ነው ያሉት ሰብሳቢው፤ አንድ የሚያደርጉ ጉዳዮች ላይ ልናተኮር ይገባል ብለዋል።   ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል የአዲስ ትውልድ ፓርቲ ተወካይ አቶ ሰለሞን ታፈሰ በበኩላቸው ፓርቲዎች ትብብርን በማጠናከር ለሀገር የምናበረክተውን አስተዋጽኦ የበለጠ ልናጎላ ይገባል ነው ያሉት።   የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ ፓርቲ (ኢዜማ) ተወካይ ዶክተር ሙሉዓለም ተገኘወርቅ በበኩላቸው በኢትዮጵያ ከዚህ በፊት የነበሩ የፖለቲካ ስብራቶች ለበርካታ ችግሮች መነሻ መሆኑን ጠቅሰው የፖለቲካ ስብራቶች መጠገን ላይ መረባረብ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል።   የሲዳማ አርነት ንቅናቄ ተወካይ አቶ ለገሰ ላንቃሞ ፤ሠላም የሁሉ ነገር መሰረት ነው ለዘላቂ ሠላም ግንባታ ሥራው ስኬታማ እንዲሆን በጠረጴዛ ዙሪያ የመወያየት ልምዳችን ይበልጥ ሊዳብር ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።    
የኢኮኖሚ ሪፎርም ግቦችን እውን ለማድረግ የሚደረገውን ጥረት ለማሳካት በጠንካራ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ የውጭ ኢንቨስትመንትን መሳብ ይገባል
Jun 10, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 3/2017(ኢዜአ)፦የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ሪፎርም ግቦችን እውን ለማድረግ የሚደረገውን ጥረት ለማሳካት በጠንካራ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ የውጭ ኢንቨስትመንትን መሳብ እንደሚገባ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የመሪዎችና ባለሙያዎች ስብሰባ "አዳዲስ መዳረሻዎችን ማሰስ፣ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲ አንቀሳቃሽ" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው።   የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሀደራ አበራ እንዳሉት፤ መድረኩ ለውጭ ጉዳይ ስራዎች መሰረት የሆነውን የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ለማጠናከር ያግዛል፡፡ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ በሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያዎች የተፈጠሩ ምቹ የኢንቨስትመንት እድሎችን ከሀገር ውስጥ ባለፈ የውጭ ኢንቨስተሮች እንዲጠቀሙባቸው የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ አቅሞችን ከዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ጋር በንግድ ኢንቨስትመንት እና በሌሎች ዘርፎች ለማስተሳሰር ጠንካራ ዲፕሎማሲ መፍጠር ይገባል ብለዋል፡፡ ለዚህ ደግሞ የኢትዮጵያን ዕምቅ አቅም ለውጭ ባለሀብቶችና ኢንቨስተሮች በሚገባ ማስተዋወቅ የሚያስችል ዘመኑን የዋጀ ዲፕሎማሲያዊ እንቅስቃሴ ማድረግ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም ጠንካራ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ አቅም በመፍጠር በንግድ፣ ኢንቨስትመንት እና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ስትራቴጂያዊ አጋሮችን ማሰባሰብ ይገባል ብለዋል፡፡ ለሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያው ስኬታማነት የውጭ ባለሀብቶች እና ኩባንያዎች ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን በመግለፅ፣ በዚህም በማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የተፈጠሩ ዕድሎችን በሚገባ ማሳወቅ ይገባል ብለዋል። የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ የመንግሥት ብቻ ሳይሆን የሁሉንም ተሳትፎ ይጠይቃል ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፤ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ ለማሻገር በቅንጅት መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ ለውጭ ጉዳይ ግንኙነት መሰረት መሆኑን በመጥቀስ፤ ከሀገር በቀል ሪፎርሙ የሚጠበቁ ግቦችን ለማሳካት የተጠናከረ ዲፕሎማሲ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡   የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) ኢትዮጵያ በጸጋዋ ልክ እንድትለማ አቅሟን በማስተዋወቅ ጠንካራ የኢኮኖሚ አጋሮችን መፍጠር ይገባል ብለዋል፡፡ ኮሚሽኑ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት አማራጮችን በሚገባ ለማስተዋወቅ "የኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ስትራቴጂ" ተግባራዊ ለማድረግ በዝግጅት ላይ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ አየርላንድ፣ እስራኤል እና ሌሎች የካሪቢያን ሀገሮች የኢንቨስትመንት አቅማቸውን ማሳደግ የቻሉት የተሻሉ ኢንቨስተሮች በመመልመል መሆኑን ገልጸው፣ ኢትዮጵያም በዚህ ላይ ትኩረት ማድረግ ይገባታል ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ተወዳዳሪና ተመራጭ የውጭ ኢንቨስትመንት መዳረሻ መሆኗን ጠቅሰው፣ ካላት እምቅ አቅም አንፃር ብዙ መስራት ይጠበቅብናል ነው ያሉት፡፡ ከዚህም ባለፈ በምስራቅ አፍሪካ ቀዳሚ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ፍሰት የምታስመዘገብ የኢንቨስተሮችም ፍላጎት በየጊዜው እየጨመረ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡   የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጃፋር በድሩ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ ቢዝነስ ተኮር ማድረግ የሚያስችል ተሻጋሪ የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ዘላቂነት እንዲኖረው የሚያስችል የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ መደረጉን ጠቅሰው፣ ለስኬታማነቱ ከዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በትብብር መስራት ይገባል ብለዋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ጥልቅ ምርምሮችን በማካሄድ፣ በአቅም ግንባታና ማማከር የኢትዮጵያን የውጭ ፖሊሲ ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም ለማስከበርና ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የተቀናጀ ጥረት ማድረግ ያስፈልጋል
Jun 10, 2025 131
አዲስ አበባ፤ሰኔ 3/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም ለማስከበር እና ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የተቀናጀ ጥረት ማድረግ ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ሃላፊ እና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህ ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያ ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ፣ እውነታዎችና ኃላፊነቶች ዙሪያ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችን ያሳተፈ ውይይት እየተካሄደ ነው፡፡   በውይይቱ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ሃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ፥ በኢትዮጵያ ወቅታዉ የፖለቲካ ሁኔታ፣ ዘላቂ ሰላም ግንባታ፣ የፖለቲካ ምህዳር ማስፋት እንዲሁም ቀጣናዊ ጉዳዮች ላይ ለውይይት መነሻ የሚሆን ሰነድ አቅርበው ውይይት ተደርጎበታል፡፡ ምክትል ፕሬዝዳንቱ፥ ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎችንም ባቀረቡት ሰነድ የፖለቲካ ምህዳሩን ይበልጥ ማስፋት እንደሚገባ አንስተዋል፡፡ የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም ለማስከበር እና ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የተቀናጀ ጥረት ማድረግ የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የኢኮኖሚ እና ማህበራዊ ልማትን በማፋጠን የህዝቦችን ተጠቃሚነት ማሳደግ ሌላው ቁልፍ ጉዳይ እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡ ለአካታች አገራዊ ምክክር ግቡን እንዲመታ ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ እንደሚገባም በውይይቱ ላይ ተነስቷል።
በጸጥታ ሃይሉ ጠንካራ የህግ ማስከበር ስራ እና በህዝቡ ትብብርና ተሳትፎ በክልሉ አስተማማኝ ሰላም ማስፈን ተችሏል-ኮሚሽነር ዘላለም መንግሥቴ
Jun 10, 2025 111
ባህርዳር፤ሰኔ 3/2017 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል በጸጥታ ሃይሉ ጠንካራ የህግ ማስከበር ስራ እና በህዝቡ ትብብርና ተሳትፎ በክልሉ አስተማማኝ ሰላም ማስፈን መቻሉን የክልሉ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ኮሚሽነር ዘላለም መንግሥቴ ገለጹ። የአማራ ክልል ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ ከፌዴራል የጸጥታ ተቋማት ጋር በወቅታዊ የጸጥታና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ተወያይቷል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የክልሉ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ኮሚሽነር ዘላለም መንግሥቴ እንደገለፁት በክልሉ በተከናወነው ጠንካራ የህግ ማስከበር ስራ አስተማማኝ ሰላምና ጸጥታ ሰፍኗል። በክልሉ የጸጥታ ችግር በነበረባቸው አካባቢዎች የተከናወኑ ህግ የማስከበር ስራዎች ከፍተኛ ውጤት የተመዘገበባቸው መሆኑን ገልጸው በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑንም አረጋግጠዋል። በመሆኑም መከላከያ ሠራዊት፣ የክልሉ የጸጥታ ኃይል፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ የብሔራዊ መረጃ እና ደኅንነት ባከናወኑት ቅንጅታዊ ስራ የላቀ ውጤት መመዝገቡን አንስተዋል። በክልሉ አስተማማኝ ሰላምና ደህንነት እንዲረጋገጥ በማድረግ ረገድ የጸጥታ ሃይሉ ጠንካራ ስራ እንዳለ ሆኖ የህዝቡም ጥረትና ትብብር አስደናቂ መሆኑን ኮሚሽነር ዘላለም ገልጸዋል። ከመንግስትና ከጸጥታ ኃይሉ ጎን በመቆም ሕዝቡ ያሳየው ቁርጠኝነት የሚፈለገው ውጤት መጥቷል ሱሉም ተናግረዋል። በጥምር ጦሩ እየተከናወነ ያለው የህግ ማስከበር ተግባር በአሁኑ ወቅት በክልሉ በሁሉም አካባቢ አስተማማኝ ሰላም እየተረጋገጠ መምጣቱን ተናግረዋል። በተወሰኑ ቆላማ የመተላለፊያ ቦታዎች በሚገኙ ቀበሌዎች ፅንፈኛ ኃይሉን የማፅዳት ስራው በተጠናከረ ሁኔታ እየተከናወነ እንደሚገኝም አመልክተዋል። የታጠቀው ፅንፈኛ ኃይል እየተካሄደ ያለውን ህግ የማስከበር እርምጃ መቋቋም ባለመቻሉ እርስ በእርስ ከመገዳደል አልፎ መንግስት ያስቀመጠውን የሰላም አማራጭ በመቀበል ቁጥሩ ቀላል የማይባል ኃይል እጁን እየሰጠ ይገኛል ብለዋል። ጥቂት የፅንፈኛው ኃይሉ አባላት በቅርብም ሆነ በሩቅ ካሉ ታሪካዊ ጠላቶቻችን የአገልጋይነት ተልዕኮ ተቀብለው በመመለስ የህዝቡን ሰላም ለማወክ ጥረት ቢያደርጉም በሀገር መከላከያ ሰራዊትና በክልሉ ጥምር የፀጥታ ኃይል መንቀሳቀሻ ማጣታቸውን አስገንዝበዋል። የክልሉ ህዝብም ሰላም የህልውና ጉዳይ መሆኑን በመረዳት ከፀጥታ ሃይሉ ጎን በመሰለፍ መረጃና ጥቆማ በመስጠት ያልተቆጠበ ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝም አስታውቀዋል። በክልሉ በቀጣይ የሚካሄደው የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የሰላም ኮንፈረንስ እና ሌሎችም ወቅታዊና መደበኛ የስራ እንቅስቃሴዎች በሰላም እንዲካሄዱ አስፈላጊው ሁሉ ዝግጅት ተደርጎ ወደ ስራ መገባቱን አረጋግጠዋል። በውይይት መድረኩ የሀገር መከላከያ ሠራዊት እና የፌዴራል ፖሊስ ከፍተኛ መኮንኖች፣ የክልሉ የፖሊስ ሃላፊዎች እና ሌሎችም የሚመለከታቸው አካላት ተገኝተዋል።   በሀገር መከላከያ ሰራዊት የመቶ አንደኛ አየር ወለድ ክፍለጦር ምክትል አዛዥ ሌተናል ኮሎኔል አየልኝ አስናቀ፤ የክልሉ ህዝብ በፅንፈኛ ኃይሉ እያደረሰ ያለውን ግፍና በደል በቅጡ በመረዳት ከፀጥታ ኃይሉ ጎን በመቆም ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን የላቀ ሚና መወጣቱን አንስተዋል። ፅንፈኛ ኃይሉ መንገድ በመዝጋት፣ በእገታና ግድያ በመፈፀም በህዝቡ ዘንድ ጉዳት ሲያደርስ መቆየቱን አስታውሰው አሁን ላይ ጠንካራ እርምጃ የተወሰደበት መሆኑን ተናግረዋል።   የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያ ኃላፊ ኮማንደር ዋለልኝ ቢምረው በበኩላቸው በተሰሩ ስራዎች የከተማዋ ሰላም እየተረጋገጠና ይበልጥ አስተማማኝ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል። በፅንፈኛ ኃይሉ ላይ በተወሰደ እርምጃ 286 የታጠቀ የፅንፈኛ ኃይሉ አባላትና በዕገታ ወንጀል የተሰማሩ 33 ግለሰቦች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም የከተማውን ሰላም ከማስጠበቅ ጎን ለጎን የተጀመሩ የልማት ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉና የሚካሄዱ ኮንፈረንሶች፣ ክልልና ሀገር አቀፍ ፈተናዎች በሰላም እንዲጠናቀቁ በቅንጅት እየተሰራ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም