ፖለቲካ
በምስራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወረዳ ሥላሴ ገዳም መሽገው መንግሥትን በትጥቅ ትግል ለመጣል ሲንቀሳቀሱ በነበሩት እስክንድር ነጋና ግብረዓበሮቹ ላይ በተወሰደው እርምጃ ክልሉን የማተራመስ ሴራቸው መክሸፉን የጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል አስታወቀ
Jun 3, 2023 90
በምስራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወረዳ ሥላሴ ገዳም መሽገው መንግሥትን በትጥቅ ትግል ለመጣል ሲንቀሳቀሱ በነበሩት እስክንድር ነጋና ግብረዓበሮቹ ላይ በተወሰደው እርምጃ ክልሉን የማተራመስ ሴራቸው መክሸፉን የጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል አስታወቀ አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ)፦ በምሥራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወረዳ የሚገኘውን የሥላሴ ገዳም ከለላ በማድረግ መንግሥትን በትጥቅ ትግል ለመጣል ሲንቀሳቀሱ በነበሩ ጥቂት ጽንፈኛ ኃይሎች ላይ በተወሰደው እርምጅ በእስክንድር ነጋና በግብረዓበሮቹ ለውጊያ ሲውል የነበረው ምሽግ መሰበሩንና በ200 ታጣቂዎችም ላይ እርምጃ መወሰዱን የጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል አስታውቋል፡፡ የታጣቂ ቡድኑ መሪና አስተባባሪ የነበረው እስክንድር ነጋና ጥቂት ግብረዓበሮቹ ከአካባቢው ለመሰወር ቢሞክሩም በዋናነት የመከላከያ ሠራዊት እንዲሁም የአማራ ክልል የጸጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር ለማዋል እግር በእግር በመከታተል የተቀናጀ ኦፕሬሽን እያካሄዱ መሆኑንም ግብረ ኃይሉ ገልጿል፡፡ የጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል ለመገናኛ ብዙኃን በላከው መግለጫ፤ ባልደራስ በሚል የፖለቲካ ፓርቲ ሽፋን ሲንቀሳቀስ የቆየው እስክንድር ነጋ የተባለው ግለሰብ የሐሳብ የበላይነትን በማረጋገጥ ዓላማውን ማሳካት ሲሳነው በአዲስ አበባ ከተማ በተለያዩ ጊዜያት ሁከትና ብጥብጥ ለመፍጠር ሲሞክር እንደነበር አስታውሷል፡፡ ግለሰቡ ይህ እንዳልተሳካለት ሲያውቅ፤ መንግሥትን በኃይል ለመጣል በማቀድ የአማራ ሕዝባዊ ግንባር የተባለ አደረጃጀት በመፍጠር ሽመልስ ስማቸው፣ ሰውመሆን ወረታውና መንበሩ ካሴ ከተባሉ ግብረዓበሮቹ እንዲሁም ከሌሎች ጥቂት የክልሉ ጽንፈኛ ኃይሎች ጋር በመቀናጀትና በህቡዕ በመንቀሳቀስ ታጣቂዎችን ሲመለምል፣ ሲያደራጅና ስምሪት ሲሰጥ እንደነበር መግለጫው ጠቁሟል። ግንባሩን በሀገር ውስጥ ራሱ ሲመራ በውጭ ደግሞ ሻለቃ ዳዊት ወ/ጊዮርጊስ የተባለ ግለሰብ ያስተባብራል ያለው መግለጫው፤ ሁለቱ በፈጠሩት ትስስር በክልሉ የትጥቅ ትግል በማድረግ ሕዝቡን ወደማያባራ ጦርነት ለማስገባት ሲንቀሳቀሱ መቆየታቸውንም የጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል ማረጋገጡን አመልክቷል፡፡ መሠረቱን ምዕራብ ጎጃም ቡሬና አባይ በረሃ አካባቢ አድርጎ ሲንቀሳቀስ የነበረው ግለሰቡ የሃይማኖት ሽፍንና እንደ ከለላ ለመጠቀም ከሌሎች የቡድኑ ታጣቂዎች ጋር ወደ ምሥራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወረዳ በማቅናት ከሁለት ዓመት በፊት ጀምሮ በሥላሴ ገዳም አካባቢ ምሽግ ቆፍረው መንግሥትን በትጥቅ ትግል ለመጣል በህቡዕ ሲያሴሩ እንደነበር ያመለከተው የግብረ ኃይሉ መግለጫ፤ በተለይ የገዳሙ አስተዳዳሪ የሆኑትን አባ ኤልሳን ለዚህ ሕገወጥ ተግባር ሲጠቀሙ እንደነበር ጠቅሷል፡፡ አስተዳዳሪውም ከሃይማኖቱ አስተምህሮ ውጭ በገዳሙ ውስጥ ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴ እንዲደረግ ከመፍቀድ ባሻገር ከሌሎች መነኮሳት ጋር በማበርና የጦር መሣሪያ ጭምር በማንገብ ከጽንፈኛ ቡድኑ አባላት ጋር ተሰማርተው እንደነበርም ጠቁሟል፡፡ መግለጫው አክሎም እነዚህ ጥቂት ጽንፈኛ ኃይሎች በአማራ ክልል እየተካሄደ ያለውን ሕግ የማስከበር ተልዕኮ ለማደናቀፍ በማለም የዜጎችን ሰላማዊ ሕይወት በሚያስተጓጉሉ ቅስቀሳዎችና ተግባራት ተሰማርተው መቆየታቸውን አስታውሷል፡፡ በአማራና በወለጋ አዋሳኝ አካባቢዎችም ግጭት እንዲቀሰቀስ ሲያደርጉ እንደነበርም አመልክቷል፡፡ የጥፋት ቡድኑ አባላት ሕገ ወጥ እንቅስቃሴውን እንዲያቆሙና በውይይት ወደ ሰላም እንዲመጡ ከክልል እስከ ወረዳ በሚገኙ አካላት ተደጋጋሚ ጥረት ቢደረግም አለመሳካቱን የጠቆመው መግለጫው፤ ይልቁንስ ገዳሙን ምሽግ በማድረግ በአካባቢው አስተዳደር፣ በፖሊስ፣በሚሊሻና በማኅበረሰቡ ላይ በተደጋጋሚ ጥቃት ሲፈጽሙ መቆየታቸውን አስታውቋል፡፡ በሃይማኖት ሽፋን ፖለቲካዊ አጀንዳቸውን ለማስፈጸም እንቅስቃሴ ሲያደርጉ እንደነበር መታወቁንም አመልክቷል፡፡ አነዚህ ጥቂት ጽንፈኛ ኃይሎች ከኅብረተሰቡ ባሕልና ዕሴት እንዲሁም ከሃይማኖታዊ አስተምህሮ ባፈነገጠ መንገድ በደብረ ኤሊያስ ወረዳ በሚገኘው ቅድስት ሥላሴ ገዳም ውስጥ ምሽግ በመቆፈር ሕዝቡ ቅዱስ የሚለውን ሥፍራ የጦር አውድማ በማድረግ ለማርከስ ቢጥሩም በዋናነት የሀገር መከላከያ ሠራዊት እንዲሁም የአማራ ክልል የጸጥታ ኃይሎች በመቀናጀት በወሰዱት ጥንቃቄ የተሞላበት እርምጃ ሴራው መክሸፉን ያስታወቀው የጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረኃይል፤ በታጣቂዎቹ ጥቅም ላይ ሲውሉ የነበሩ የተለያዩ ከባድና ቀላል መሣሪያዎችም በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ጠቁሟል፡፡ 200 የጽንፈኛ ቡድኑ አባላት ታጣቂዎች መደምሰሳቸውነና የቀሩትም ከመማረካቸውና ከመሸሻቸው ውጪ፤ ቡድኑ የሐሰት ፕሮፓጋንዳ በሚነዛባቸው የማኅበራዊ ትስስር ገፆች በመንግሥት ጸጥታ አካላት በገዳሙና በምዕመናን ጉዳት እንዳደረሰ ተደርጎ የሚሠራጨው መረጃ ከእውነት የራቀ መሆኑን መግለጫው አመልክቷል፡፡ የሀገር መከላከያ ሠራዊትና የአማራ ክልል የጸጥታ ኃይሎች በተቀናጀ መንገድ እርምጃ በወሰዱበት በዚህ ሕግ የማስከበር ስምሪት የአካባቢው ማኅበረሰብ መረጃ በመስጠትና በሌሎችም መንገዶች ያደረገው ትብብር የሚደነቅ መሆኑን ያመለከተው የጸጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይሉ ለዚህም ምስጋናውን አቅርቧል፡፡ በቀጣይም ክልሉ ከጥቂት ጽንፈኛ ኃይሎች ጸድቶ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንዲሰፍን ለሚደረገው ሕግ የማስከበር እንቅስቃሴ ኅብረተሰቡ የጋራ ጥረቱንና አጋርነቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
ቻይናና ኢትዮጵያ ያሏቸው የባህልና የቋንቋ ልውውጥ ለአገራቱ ግንኙነት መጠናከር ትልቅ አስተዋጽኦ  አለው - በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ዣኦ ዥዩዋን
Jun 3, 2023 125
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ)፦ ቻይናና ኢትዮጵያ ያሏቸው የባህልና የቋንቋ ልውውጥ ለአገራቱ ግንኙነት መጠናከር ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ዣኦ ዥዩዋን ገለጹ። በቻይና መንግሥት አመቻቺነት በኢትዮጵያ የቻይና ቋንቋን በዩንቨርሲቲ ደረጃ ከሚያጠኑ ኢትዮጵያዊያን እንዲሁም ቻይንኛን አንድ ክፍለ ጊዜ በሚወስዱ ከሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ ተማሪዎች ዛሬ በቻይንኛ የተለያዩ የመድረክ ሥራዎችን አቅርበዋል።   በመድረኩ ተማሪዎቹ በቻይንኛ ቋንቋ ንግግሮች፣ የቻይንኛ ሙዚቃና ስፖርት እንዲሁም ልዩ ልዩ ትዕይንቶችን በውድድር አሳይተዋል። በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ዣኦ ዥዩዋን በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት ኢትዮጵያና ቻይና በተለያዩ የትብብር መስኮች ያሏቸው ግንኙነት እየተጠናከረ ነው። ቻይናና ኢትዮጵያ ያሏቸው የባህልና የቋንቋ ልውውጥ ለአገራቱ ግንኙነት መጠናከር ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ነው አምባሳደሩ የገለጹት።   በመድረኩ በትምህርት ሚኒስቴር የዓለም አቀፋዊነትና ስኮላርሺፕ ዴስክ የተወከሉት ተረፈ በላይ በበኩላቸው ሁለቱ አገራት የረዥም ዓመታት ግንኙነት አላቸው ብለዋል። አገራቱ ያላቸው አጋርነት በተለይም በኢኮኖሚ መስክ ወደ ላቀ ደረጃ እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በሁለቱ አገራት ሕዝቦች መካከል የባህል ትስስሩ መጠናከሩ ደግሞ የአገራቱን ሁለንተናዊ አጋርነት ይበልጥ እንደሚያጠናክረው ነው ያስረዱት። በተለይም ደግሞ በአገራቱ መካከል የቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲፈጠርና ኢኮኖሚያዊ አጋርነቱን ወደ ላቀ ደረጃ እንደሚያደርሰው አብራርተዋል።   በመድረኩ ላይ ሲሳተፉ የነበሩት ተማሪዎች በበኩላቸው አንዲህ ያለው ተሞክሮ የሁለቱን አገራት ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ያደርሳል ነው ያሉት። ቢሾፍቱ ሁለተኛ ደረጃ አዳሪ ትምርት ቤት ተማሪ የሆነችው ሲያኔ ታደሰ መርሃ ግብሩ የሁለቱ አገራት ግንኙነት ለማጠናከር እድል እንደሚሰጥ ጠቁማለች። በተለይም ቻይና አሁን ላይ የኢንዱስትሪ ማዕከል መሆኗን ገልጻ በመሆኑም የቻይና ቋንቋ ማወቅ በዘርፉ ይበልጥ ተባብሮ ለመሥራት እንደሚያግዝ ተናግራለች። ሌላኛው በአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ የቻይንኛ ቋንቋ ተማሪ ናፍያድ ንጋቱ ቻይንኛ የሚማሩ ኢትዮጵያዊያን መኖራቸው እንዲሁም አማርኛ የሚማሩ ቻይናውያን መኖራቸው ትስስሩን ያጠናክራል ብሏል። በሁለቱ አገራት መካከል ግንኙነቱን ለማጠናከር የባህል ግንኙነቱ ትልቅ ጥቅም አለው ያለው ደግሞ በሀዋሳ ዩንቨርሲቲ የቻይንኛ ቋንቋ ተማሪ በረከት ደመላሽ ነው።    
ሰራዊቱ ብቃቱን የሚያሳድግበት ምቹ አካባቢ በመፍጠር የመፈጸም አቅሙን ለማሳደግ እየተሰራ ነው - ሌተናል ጄነራል ብርሃኑ በቀለ
Jun 3, 2023 75
ባህር ዳር ግንቦት 26/2015((ኢዜአ) :- የአገር መከላከያ ሰራዊት ብቃቱን የሚያሳድግበትና ዝግጁነቱን የሚያጠናክርበት ምቹ አካባቢ በመፍጠር የመፈጸም አቅሙን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የሰሜን ምዕራብ ዕዝ አዛዥ ሌተናል ጄነራል ብርሃኑ በቀለ ገለጹ። የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ በሰሜን ምዕራብ ዕዝ መቀመጫ ያከናወነውን የጥገና እና ግንባታ ስራ አጠናቆ ዛሬ ለዕዙ አስረክቧል።   የሰሜን ምዕራብ ዕዝ አዛዥ ሌተናል ጄነራል ብርሃኑ በቀለ በርክክብ ስነ-ስርዓቱ ላይ እንዳሉት የአገር መከላከያ ሰራዊት አገርን የመጠበቅ ሕገ መንግስታዊ ተልዕኮውን ለመወጣት ሁልጊዜም ዝግጁ ነው። አገርን ከማንኛውም ችግር ለመከላከል የሚያስችል በቂ ዝግጅት ለማድረግም ለሰራዊቱ ደረጃውን የጠበቀ የመኖሪያና የመዘጋጃ ካምፕ መገንባት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ሰራዊቱ በሰላም ጊዜ ተረጋግቶ የሚኖርበት፣ በስልጠናዎች ብቃቱን የሚያሳድግበትና ለተልዕኮ ዝግጁነቱን የሚያጠናክርበት ምቹ አካባቢ በመፍጠር የመፈጸም አቅሙን ለማሳደግ እየተሰራ ነው ብለዋል። የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ የዕዙ መቀመጫ የሆነውን መኮድ ካምፕ በማደስና የአጥር ግንባታ ሥራ በማከናወን ምቹ መኖሪያና የስራ ቦታ በማስረከቡ ሌተናል ጄነራል ብርሃኑ ምስጋናቸውን አቅርበዋል። የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጄነራል ደስታ አብቼ በበኩላቸው መምሪያው የሰራዊቱንና የአመራሩን የመፈጸም ብቃት የሚያሳድጉ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።   በዚህም የሬጅመንት፣ የክፍለ ጦር፣ የኮር እና የዕዝ ቢሮዎች፣ መኖሪያዎችንና ሌሎች መጠለያ ካምፖችን በመገንባት መንግስት የሰጠውን ተልዕኮ በመወጣት ላይ መሆኑን አመልክተዋል። ከአገራዊ ለውጡ ወዲህ መምሪያው 48 የውሃ ጉድጓዶችን በአገር ደረጃ በማስቆፈር ሰራዊቱ የሚገለገልባቸው ሆስፒታሎች፣ ካምፖችና መኖሪያ አካባቢዎችን ተጠቃሚ ማድረጉንም ሌተናል ጄኔራል ደስታ የተናገሩት። በመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ የኮንስትራክሽን መምሪያ ኃላፊ ብርጋዴል ጀኔራል ያደታ አመንቴ በበኩላቸው፣ ከመኮድ ካምፕ እድሳት ስራ በተጨማሪ የአጥር ግንባታ ስራ መከናወኑን ገልጸዋል።   የቢሮ ሕንጻ፣ የሎጅስቲክስ ክፍሎች፣ መዝናኛዎች እንዲሁም ለተለያየ አገልግሎት የሚውሉ አዳራሾችና የሰራዊት መኖሪያ ቤቶች ሙሉ እድሳት እንደተደረገላቸው አመልክተዋል። የሰሜን ምዕራብ ዕዝ መኖሪያ እና የመኮድ ካምፕ ጥገናና 7 ነጥብ 5 ኪሎ ሜትር የሚረዝመው የአጥር ግንባታ ስራ በ15 ወራት ጊዜ ውስጥ መከናወኑን በርክክብ ስነ ስርዓቱ ላይ ተገልጿል።  
መጪው ጊዜ ለኢትዮጵያ እና ቻይና ግንኙነት ብሩህ ነው - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን
Jun 3, 2023 82
አዲስ አበባ ግንቦት 26/2015 (ኢዜአ)፦ “መጪው ጊዜ ለኢትዮጵያ እና ቻይና ግንኙነት ብሩህ ነው” ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ገለጹ። የሁለቱን አገራት ትብብር ሁሉን አቀፍ እና ስትራቴጂካዊ ነውም ብለዋል። በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የተመራ ከፍተኛ የመንግስት የልዑካን ቡድን በቅርቡ በቻይና ይፋዊ የስራ ጉብኝት ማድረጉ ይታወቃል። አቶ ደመቀ ከጉብኝቱ ጎን ለጎን ከቻይናው ሲ ጂ ቲ ኤን 'ሃይ ቶክ' ከተሰኘው ፕሮግራም ጋር ቆይታ አድርገዋል። በቆይታቸውም የኢትዮጵያ እና የቻይና የሁለትዮሽ ትብብር ጠንካራ እና ወዳጅነት ላይ መሰረት ያደረገ ነው ያሉት አቶ ደመቀ፤ ሁለቱ አገራት ያልተነኩ እድሎችን ለመጠቀም ያላቸው ፍላጎት የወደፊቱን የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ብሩህ እንደሚያደርገው ገልጸዋል። የአገራቱ ግንኙነት ሁሉን አቀፍ፣ ስትራቴጂካዊ እና የጋራ ትብብር ያለው መሆኑ ቻይና ለኢትዮጵያ የረጅም ጊዜ የኢኮኖሚ ትልሞች ድጋፍ ለማድረግ ጥሩ መሰረት እንደጣለ አመልክተዋል። የኢትዮጵያ እና ቻይና ግንኙነት ከሁለትዮሽ ትብብራቸው ባለፈ የኢኮኖሚ ትስስር ላይ የሚያተኩረው የደቡብ-ደቡብ ትብብር ጽንሰ ሀሳብ ማሳያ ነው ያሉት አቶ ደመቀ ይህም ለተቀረው የአፍሪካ አህጉር የልማት ሕልሞች ምሳሌ እንደሚሆን ተናግረዋል። የቤልት ኤንድ ሮድ ኢኒሼቲቭ እና የቻይና-አፍሪካ ትብብር ፎረም(ፎካክ) በአፍሪካ እና ቻይና ትብብር አፍሪካውያን ሰላማዊ እና የበለጸገች አፍሪካን እውን ለማድርግ ሕልማቸውን እንዲያሳኩ የሚያግዙ ማዕቀፎች መሆናቸውን ነው አቶ ደመቀ ያስረዱት። የቻይናው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኪን ጋንግ በኢትዮጵያ ያደረጉት ጉብኝት እና የቻይና የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ አምባሳደር ሹ ቢንግ የሰላም ጥረቶች ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የረጅም ጊዜ ግንኙነት ለማጠናከር ያላትን ቁርጠኝነት የሚያሳይ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ የሰላም ሂደቱን ለማጽናት በቁርጠኝነት እየሰራች መሆኑን ገልጸው በሰላም ሂደቱ የቻይና የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክን ጨምሮ የሁሉንም ባለድርሻ አካላት ሚና እንደምታደንቅ ገልጸዋል። ሌሎችም በአፍሪካ ችግሮች አፍሪካዊ መፍትሔ መርህ በመመራት ድጋፋቸውን እንዲያደርጉ አቶ ደመቀ ጥሪ ማቅረባቸውን የሲጂቲኤን ዘገባ ያመለክታል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ መለስ ዓለም ከትናንት በስቲያ በውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ መስክ በተከናወኑ አበይት ጉዳዮች ላይ በሰጡት ሳምንታዊ መግለጫ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በቻይና ያደረጉት ጉብኝት የኢትዮጵያና የቻይና ወዳጅነትና ትብብርን ከፍ ያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። አቶ ደመቀ በቆይታቸውም ከቻይና መንግስት ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች እንዲሁም ከባለሀብቶች ጋር ውይይት ማድረጋቸውን ገልጸው ውይይቶቹ የሁለቱን አገራት ግንኙነትና ወዳጅነት የበለጠ ለማጠናከር እድል የፈጠሩ መሆናቸውን አመልክተዋል። አቶ ደመቀ በቻይና ባደረጉት ጉብኝት ከቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኪን ጋንግ፣ከቻይና ምክትል ፕሬዝዳንት ሃን ዤንግ እና ከሌሎች ባለስልጣናት ጋር የሁለትዮሽ እና የባለ ብዙ ወገን ግንኙነታቸውን ትብብራቸውን ማጠናከር በሚችሉባቸው ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርገዋል። በተጨማሪም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በቤጂንግ የተገነባውን የኢትዮጵያ ኤምባሲ መርቀው መክፈታቸው የሚታወስ ነው።
በኢጋድ ቀጣና ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት እንዲፈጠር በሚደረገው ጥረት ውስጥ መገናኛ ብዙኃን ጉልህ ድርሻ አላቸው--አምባሳደር መለስ ዓለም
Jun 2, 2023 145
አዲስ አበባ ግንቦት 25/2015(ኢዜአ):-በምሥራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ቀጣና ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲፈጠር በሚደረገው ጥረት የመገናኛ ብዙኃን ሚና የላቀ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር መለስ ዓለም ገለፁ። አምባሳደር መለስ ይህን የገለፁት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከኢጋድ ጋር በመተባበር የፀጥታ እና ደህንነት ጉዳዮች ዘገባዎች እና የመገናኛ ብዙኃን ሚና በሚል ከተለያዩ መገናኛ ብዙኃን ለተውጣጡ ጋዜጠኞች በተዘጋጀ ሥልጠና ላይ ነው። ቃል አቀባዩ "ለዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት የመገናኛ ብዙኃን ሚና" በሚል የመነሻ ጽሑፍ አቅርበዋል። አምባሳደር መለስ የመገናኛ ብዙኃን በኢጋድ እንደ ቀጣና እና እንደ አገር በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ከፍተኛ ሚና እንዳላቸው የዓለም አቀፍ ተሞክሮዎችን በማቅረብ አብራርተዋል። የሰላም እና ፀጥታ ጉዳዮች ምሁሩ ዶክተር ዮናስ አዳዬ የኢጋድ ቀጣና ወቅታዊ የጂኦ ፖለቲካ አዝማሚያ ላይ ያተኮረ ማብራሪያ አቅርበዋል። ዶክተር ዮናስ በገለፃቸው የአፍሪካ ቀንድ የተለያዩ ፍላጎቶች ከሚንፀባረቁባቸው ቀጣናዎች መካከል አንዱ መሆኑን አንስተዋል።   መገናኛ ብዙኃን መረጃዎችን ለሕዝብ ከማድረሳቸው አስቀድመው የቀጣናውን ትክክለኛ ገፅታ ከተለያዩ መመዘኛዎች አንፃር መፈተሽ እንዳለባቸው አብራርተዋል። በኢጋድ ክልል ውስጥ የግጭት እና የፀጥታ ጉዳዮች ተፈጥሮ እና ተለዋዋጭነት እንዲሁም በኢትዮጵያ የድህረ ግጭት የሰላም ግንባታን በሚመለከትም ዶክተር ዮናስ ገለፃ አድርገዋል። የሥልጠናው ተሳታፊዎችም የተለያዩ ጥያቄዎች እና አስተያየቶችን በማንሳት ሰፊ ውይይት ተደርጎበታል።            
አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ በኢትዮጵያ እና በኩዌት መካከል የሰራተኛ ስምሪት ስምምነት እንዲፈረም ጠየቁ
Jun 1, 2023 150
አዲስ አበባ ግንቦት 24/2015 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እና በኩዌት መካከል የሰራተኛ ስምሪት ስምምነት በአጭር ጊዜ እንዲፈረም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ ጠየቁ ሚኒስትር ዴኤታው ዛሬ በኢትዮጵያ የኩዌት አምባሳደር ናይፍ ሃኘስ አል ኦይታይቢን በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል። አምባሳደር ምስጋኑ በውይይቱ ላይ በኢትዮጵያ እና በኩዌት መካከል የሰራተኛ ስምሪት ስምምነት በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲፈረም የሚደረገው ዝግጅት እንዲፋጠን ጠይቀዋል። የሁለቱ አገራት የጋራ የሚኒስትሮች ኮሚሽን ስብሰባ በሚጀመርበት ሁኔታ ዙሪያም ውይይት ያደረጉ ሲሆን ከወዲሁም አስፈላጊ ዝግጅት ማድረግ እንደሚገባ ጠቁመዋል። በሰሜን ኢትዮጵያ በነበረው ጦርነት የተጎዱ አካባቢዎችን መልሶ ለመገንባት እና ለማቋቋም እየተደረገ ያለውን ጥረት የኩዌት መንግስት እንዲደግፍም አምባሳደር ምስጋኑ ጥሪ አቅርበዋል። በኢትዮጵያ የኩዌት አምባሳደር ናይፍ ሃኘስ አል ኦይታይቢ በበኩላቸው በሁለቱ ሃገራት መካከል የሰራተኛ ስምሪት ስምምነት በአጭር ጊዜ እንዲፈረም የኩዌት መንግስት እየሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ እና የኩዌት የጋራ የሚኒስትሮች ኮሚሽን ስብሰባው እንዲጀመር አስፈላጊውን ጥረት እንደሚያደርጉም ገልጸዋል።
ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር በሚደረገው ጥረት ውስጥ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ሚናቸውን ሊወጡ ይገባል - የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር 
Jun 1, 2023 148
አዲስ አበባ ግንቦት 24/2015 (ኢዜአ):- ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር በሚደረገው ጥረት ውስጥ የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች የሚጠበቅባቸውን ሚና በአግባቡ መወጣት እንዳለባቸው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለጸ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከምስራቅ አፍሪካ የልማት በየነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) ጋር በመተባበር ለአገር ውስጥና ለውጭ ጋዜጠኞች ለሁለት ቀናት የሚቆይ ሥልጠና እየሰጠ ነው። ሥልጠናው መገናኛ ብዙኃን ጸጥታና ደኅንነት በማረጋገጥ እንዲሁም ድንበር ዘለል የጸጥታ ሥጋት በመከላከል ሚናቸውን ማጎልበት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ትኩረት አድርጓል ተብሏል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ መለስ ዓለም በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር በሚደረገው እንቅስቃሴ ዲፕሎማቶች ብቻ ሳይሆን ጋዜጠኞችም ኃላፊነት አለባቸው ብለዋል። በመሆኑም ጋዜጠኞች የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት መወጣት እንዳለባቸው ገልጸው በተለይም ደግሞ ትክክለኛ መረጃዎችን በማሰናዳት ለኅብረተሰቡ ተደራሽ ማድረግ ይኖርባቸዋል ነው ያሉት።   የውጭ ጉዳይ ሚንስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ምክትል ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር ጀማላዲን መሃመድ በበኩላቸው ሥልጠናው ጋዜጠኞች በጸጥታ ጉዳዮች ያላቸውን ግንዛቤ ከፍ የሚያደርግ ነው ብለዋል። በተለይም በግጭትና በፀጥታ ጉዳዮች ላይ ኃላፊነት በተሞላበት አኳኋን እንዲሰሩ እንዲሁም ትክክለኛና ሚዛናዊ ዘገባዎችን ለማቅረብ አስፈላጊውን እውቀትና ክህሎት ለማዳበር የሚረዳ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የኢጋድ አባል አገራት ድንበር ተሻጋሪ የጸጥታ ሥጋቶችን ለመቅረፍ የአባላትን አቅም ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት ጋዜጠኞች የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ እንደሚረዳ ገልጸዋል። የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግሥታት ባለሥልጣን (ኢጋድ) የጸጥታና ደኅንነት ዘርፍ ዳይሬክተር ኮማንደር አበበ ሙሉነህ፤ የምስራቅ አፍሪካ ቀጣና በበርካታ ድንበር ዘለል የጸጥታና ደኅንነት ሥጋቶች ያሉበት መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም መገናኛ ብዙኃን በቀጠናው የሚያጋጥሙ የጸጥታ፣ ደኅንነትና ወንጀል ሥጋት በአግባቡና በትክክለኛው መንገድ በመገንዘብ ገጽታ የሚገነቡና ብሔራዊ ጥቅምን የሚያስከብሩ ሥራዎችን በትኩረት መሥራት አለባቸው ነው ያሉት። በአፍሪካ ቀንድ ሰላምና ደኅንት ማረጋገጥ ብዙኃኑን ያሳተፈ ሁለገብ ሥራን የሚጠይቅ በመሆኑ በዚህ ረገድ የመገናኛ ብዙኃን የድርሻቸውን ጉልህ ሚና ሊወጡ እንደሚገባ ተጠቁሟል። የመገናኛ ብዙኃን ግጭትን መከላከል ብቻ ሳይሆን በድህረ ግጭት የሰላም ግንባታ እንዲሁም ደግሞ ሰላም በዘላቂነት እንዲረጋገጥ የሚጠበቅባቸውን ሃላፊነት መወጣት እንዳለባቸው ነው ያሳሰቡት።            
አገራዊ ምክክሩ የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት መደላድል የሚፈጥር ነው - የድሬዳዋ ሕብረተሰብ ተወካዮች  
May 31, 2023 152
ድሬዳዋ ግንቦት 23/2015 (ኢዜአ):- አገራዊ የምክክር መድረኩ ብሔራዊ መግባባት በመፍጠርና አንድነትን በማጠናከር የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት መደላድል እንደሚፈጥር የድሬዳዋ ሕብረተሰብ ተወካዮች ገለጹ። የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን በአገራዊ የምክክር ሂደት ላይ አጀንዳ ለማሰባሰብ ስለሚከናወኑ ተግባራትና የውይይት ተሳታፊዎች ልየታን አስመልክቶ በድሬዳዋ ለሁለት ቀናት ያዘጋጀው ስልጠና ተጠናቋል ። በስልጠናው ላይ የተሳተፉ የድሬዳዋ ሕብረተሰብ ተወካዮች እንዳሉት በአገር አቀፍ ደረጃ የሚካሄደው የምክክር መድረክ ብሔራዊ መግባባት የሚፈጥር ወሳኝ የሽግግር ምዕራፍ ነው። ከድሬዳዋ መምህራን ማህበር የመጡት መምህርት ሙሉካ ሁሴን ስልጠናው በቀጣይ በሚካሄደው አገራዊ ምክክር ተሳታፊዎችን የመለየት ሂደት ተአማኒነትና አሳታፊነትን ያሟላ ለማድረግ እንደሚያስችል ገልጸዋል። “በአገር ደረጃ የሚካሄደው የምክክር መድረክ በዜጎች መካከል መቀራረብ እና አንድነትን በማጠናከር የኢትዮጵያን ሁለንተናዊ ከፍታ ለማረጋገጥ ያስችላል” ብለዋል። አገራዊ የምክክር መድረክ አገራዊ መግባባት ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የድሬዳዋ የፓለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ ዮናስ በትሩ ናቸው። በሰከነ መንፈስ መወያየት ለአገር ዘላቂ ሰላምና እድገት ጠቀሜታው የጎላ መሆኑንና የጋራ ምክር ቤቱ በቀጣይ የሚካሄዱ የምክክር ተግባራት ውጤታማ እንዲሆኑ ይሰራል ብለዋል። የድሬዳዋ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ጥምረት ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አንድነት ዘነበ "ኢትዮያዊያን የሚያካሂዱት ምክክር አገራዊ አንድነትን ለማጠናከር መሰረት የሚጥል ነው" ብለዋል። የምክክር መድረኩ ኢትዮጵያዊያን በራሳቸው አጀንዳዎች ላይ መግባባት የሚፈጥሩበት ብቻ ሳይሆን አንድነትና አቅም መፍጠር የሚያስችላቸው መሆኑን አመልክተዋል።   የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር መሐሙድ ድሪር እንዳሉት ኮሚሽኑ በሚያከናውነው የተሳታፊዎች ልየታ የተለያዩ ተቋማት እና ባለድርሻ አካላት የሂደቱን ግልጸኝነት ፣አሳታፊነትና ተአማኒነት የመታዘብና የማረጋገጥ ሚና እንዳላቸው ገልጸዋል። የምክክር መድረኩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ጨምሮ ሁሉንም የሚያሳትፍ በመሆኑ ብሔራዊ መግባባት በመፍጠር ኢትዮጵያን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማሻገር መሰረት የሚጥል ነው ብለዋል። በሰከነ መንገድ በመወያየት የጋራ አገራዊ መግባባት በመፍጠር ኢትዮጵያን ለማሻገር እንደሚያስችል አመልክተዋል።  
ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ እየሰሩ እንደሚገኙ የአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች የሚኖሩ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች ገለጹ
May 31, 2023 127
ደብረ ብርሃን ግንቦት 23 / 2015 (ኢዜአ):- አብሮነትን በማጠናከር የአካባቢያቸውን ሰላም ዘላቂ ለማድረግ እየሰሩ እንደሚገኙ በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች አዋሳኝ አካባቢዎች የሚኖሩ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎች አስታወቁ። በአማራ ክልል የአንጎላላ ጠራ ወረዳ እና በኦሮሚያ ክልል የቅንቢቢት ወረዳ ነዋሪዎች በአካባቢያቸው ዘላቂ ሰላምን ማስፈንና ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የጋራ ውይይት ዛሬ አካሄደዋል። ከአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን አጎላላ ጠራ ወረዳ ተሳታፊ የሆኑት መላከ መዊዕ ቀሲስ ገዛኸኝ ኃይሉ እንደገለጹት፤ የአማራና የኦሮሞ ሕዝብ በአንድነት፣ በፍቅር እና በመተሳሰብ የሚኖር ነው። ለሕዝቡ ሰላምን፣ ፍቅርን፣ አንድነትንና መተሳሰብን መሰረት አድርገው በማስተማር የአካባቢያቸው ሰላም በዘላቂነት እንዲጠበቅ እንደሚሰሩ ተናግረዋል። ከኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ቅንቢቢት ወረዳ የመጡት ቄስ ተሰማ በላቸው በበኩላቸው በሕዝቦች መካከል ፍቅርና ሰላም ጸንቶ እንዲዘልቅ ወጣቶችን እያስተማርን ነው ብለዋል። የሕዝቦች አብሮ የመኖር እሴት እንዲጎለብትና ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን በማስተማር የበኩላቸውን ሚና እየተወጡ መሆኑን ገልጸዋል።   ከቅንቢቢት ወረዳ የመጡት የአገር ሽማግሌ አቶ ተስፋዬ ግርማ በበኩላቸው በአካባቢው የሚኖሩ የኦሮሞ እና የአማራ ህዝቦች ከትውልድ ትውልድ የተሻገረ የጋራ ታሪክና እሴት እንዳላቸው አውስተዋል። "የብሔር ልዩነት ሳይገድበን አብረን የምንኖር ሕዝቦች በመሆናችን የጀመርነውን የጋራ እድገት፣ ልማትና ዘላቂ ሰላም የማረጋገጥ ጥረት አጠናከክረን እንቀጥላለን" ብለዋል። በአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን አንጎለላ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት የአገር ሽማግሌ አቶ ተስፋዬ ሞገስ በበኩላቸው ከኦሮሚያ ክልል አዋሳኝ ወረዳ ሕዝቦች ጋር በፍቅርና በሰላም የምንኖረው በመማከርና በመወያየት ነው ሲሉ ገልጸዋል። አለመግባባቶች ሲኖሩ የአገር ሽማግሌዎችና የሀይማኖት አባቶች ጋር በመመካከር እየፈቱ እንደሚገኝና በዚህም የአካባቢው ሰላም ተጠብቆ መቆየቱን ተናግረዋል። "የአካባቢያችንን ሰላም ለማደፍረስ የሚጥሩ ኃይሎችን እኩይ ሴራ ቀድሞ በማክሸፍ ሰላሙ ጽንቶ እንዲዘልቅ በጋራ የጀመርነው ውይይትና ምክክር ተጠናክሮ ይቀጥላል" ብለዋል። የውይይቱ ተሳታፊዎች ከአካባቢያቸው ባለፈ በአገር አቀፍ ደረጃ ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ መንግስት የሚያደርገውን ጥረት በመደገፍ የድርሻቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል።    
የሲዳማ ክልል የህዝብ አደረጃጀቶች የህዝብ ጥያቄዎች ለአገራዊ ምክክር መድረክ እንዲቀርቡ ሀላፊነታቸውን እንደሚወጡ ገለጹ 
May 31, 2023 114
ሀዋሳ ግንቦት 23/2015 (ኢዜአ) የህዝብ ጥያቄዎች ለአገራዊ ምክክር መድረክ እንዲቀርቡ ሀላፊነታቸውን እንደሚወጡ በአገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ በተባባሪነት የተለዩ የሲዳማ ክልል የህዝብ አደረጃጀቶች አስታወቁ። ኮሚሽኑ በተሳታፊ ልየታና አጀንዳ መረጣ ላይ ለሚሳተፉ ተባባሪ አካላት በሀዋሳ ከተማ ባዘጋጀው ስልጠና ላይ የተሳተፉ የሴቶች፣ አካል ጉዳተኞች፣ የእድርና ፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ለኢዜአ በሰጡት አስተያየት የኮሚሽኑ ስራ በስኬት እንዲጠናቀቅ የዜጎች ያልተቆጠበ ተሳትፎ ያስፈልጋል። በመሆኑም በምክክሩ የሚሳተፉ የህብረተሰብ ተወካዮችን የመምረጥ ሂደቱ የተሳካ እንዲሆን ሃላፊነታቸውን በአግባቡ እንደሚወጡ ገልጸዋል። በሲዳማ ክልል ሴቶች ማህበር የሲቪክ ማህበረሰብ ተወካይ ወይዘሮ ዘውዲቱ ጥላሁን በአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ለሚከናውነው ታላቅ ተልእኮ በተባባሪነት መመረጣቸው ከፍተኛ ሃላፊነት እንደሆነ ገልጸዋል። ይህን ሃላፊነት በአግባቡ በመወጣት እስከታችኛው መዋቅር ድረስ ያሉ ሴቶች ድምጽ እንዲሰማ ለማድረግ የሴቶችን ተሳትፎ ለማጠናከር እንደሚሰሩ ተናግረዋል። በሰላም ማጣት የበለጠ ተጎጂ ከሚሆኑት ማህበረሰብ ክፍሎች ሴቶች መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በሂደቱ ሴቶች በንቃት እንዲሳተፉ ለማስቻል እንሰራለን ብለዋል። የመልጋ ወረዳ አካል ጉዳተኞች ማህበር ሰብሳቢ አቶ ሃየሶ ሃሶ በበኩላቸው በብሄራዊ ምክክር ሂደቱ የአካል ጉዳተኞች ተሳትፎ እንዲኖር መደረጉ በርካታ ችግሮችን ለመቅረፍ ያስችላል ብለዋል።   በስልጠና መድረኩ ያገኙትን ግንዛቤ ተጠቅመው በምክክር መድረኩ ተገቢውን ሃሳብ ሊያንሸራሽሩ የሚችሉ ተወካዮችን በመምረጥ ከብሄራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ጋር እንደሚሰሩ ተናግረዋል። ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን በመፍታት የሀገርን ህልውና ለማስቀጠል የብሄራዊ ምክክሩ አስፈላጊነት በዜጎች ቅቡልነት ያገኘ ነው ያሉት ደግሞ የሲዳማ ክልል የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ተወካይ አቶ ሃብተማርያም አብዩ ናቸው። የማያስማሙን ጉዳዮች ቢኖሩ እንኳን በአገር ሰላምና አንድነት ላይ ባለመደራደር የንግግር ባህልን ማሳደግና ከችግሩ ለመውጣት መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል። በሀዋሳ ከተማ የመሀል ክፍለ ከተማ እድር ተወካይ አቶ መስፍን ዘውዴ በበኩላቸው አገራዊ ምክክሩ ለግጭት መንስኤ እየሆኑ ላሉ በርካታ ችግሮች መፍትሄ የሚሰጥ በመሆኑ ብርቱ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል። እድሮች የተለያየ ህብረተሰብ ክፍል የሚሳተፍባቸው እንደመሆናቸው መጠን ለሀገር ጠቃሚ ሃሳቦችን ማመንጨት እንደሚችሉ አመልክተዋል። በመሆኑም የተለያዩ ህብረተሰብ ክፍሎችን የሚወክሉ አካላትን በመምረጥ የህዝቡን ችግር በተገቢው የሚያሳይ አጀንዳ ለመምረጥ ሃላፊነታቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። ብሄራዊ ምክክር ኮሚሽን በሲዳማ ክልል በአጀንዳ ማሰባሰብና ምክክር ላይ የሚሳተፉ አባላትን ለሚመለምሉ ተባባሪ አካላት በሀዋሳ ስልጠና መስጠቱ ይታወሳል።
ብልፅግና ፓርቲ በሰጠው ጠንካራና ቅቡልነት ያለው አመራር የሀገረ መንግስት ግንባታን የሚያፋጥኑ ስራዎች ተከናውነዋል - የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህ
May 31, 2023 137
አዲስ አበባ ግንቦት 23/2015 (ኢዜአ)፦ብልፅግና ፓርቲ በሰጠው ጠንካራና ቅቡልነት ያለው አመራር የሀገረ መንግስት ግንባታን የሚያፋጥኑ ስራዎችን ማከናወን መቻሉን የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳን አቶ አደም ፋራህ ገለጹ። ፓርቲው የተጀመሩ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ዲፕሎማሲያዊ ስራዎች በስኬት እንዲቀጥሉ የፓርቲውን አመራር የማጥራት፣ የማጠናከርና የመገንባት ስራ አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አደም ፋራህ የብልጽግና ፓርቲ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ለሁለት ቀናት ሲያካሂድ በቆየው መደበኛ ስብሰባ ያስቀመጣቸው አቅጣጫዎችና ነገ የሚጀመረውን የፓርቲው ማዕከላዊ ኮሚቴ አባላት ስብሰባ በማስመልከት ለኢዜአ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና በዲፕሎማሲያዊ ዘርፎች የተመዘገቡ ውጤቶችን ገምግሞ የቀጣይ አቅጣጫዎችን አስቀምጧል ብለዋል፡፡ በፖለቲካው ዘርፍ የጋራ መግባባት ያልተደረሰባቸው መሰረታዊ ሀገራዊ ጉዳዮችን በምክክር ኮሚሽኑ አማካኝነት በዴሞክራሲያዊ መንገድ ለመፍታት የተጀመረው ጥረት መልካም መሆኑ ተገምግሟል ነው ያሉት፡፡ የብልጽግና ፓርቲም ሁሉንም አሳታፊ ውይይት እንዲደረግ እና የጋራ ብሔራዊ መግባባት ላይ እንዲደረስ እንደ አንድ ፓርቲ የበኩሉን ሚና እንዲያበረክት አቅጣጫ መቀመጡን አንስተዋል፡፡ ፓርቲው በኢትዮጵያ የዲሞክራሲ ስርዓትን ለማንበር በርዕዮትና በፖሊሲ የሚለዩትን የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች በመንግስት መዋቅር ውስጥ በማሳተፍ የትብብር መንፈስ እንዲፈጠር አድርጓል፤ ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ዘላቂና አወንታዊ ሰላም ለመፍጠር ለህዝብ ጥቅም የቆሙ ነፃና ገለልተኛ የጸጥታና ደህንነት እንዲሁም የዴሞክራሲ ተቋማትን በመገንባት አመርቂ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል፡፡ የትጥቅ ትግል ሲያካሂዱ ከነበሩ አካላት ጋር ዘመናዊና ባህላዊ የግጭት አፈታት ዘዴዎችን ያጣመረ ውይይት በማካሄድ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ጥረት መደረጉ በስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው በአዎንታዊነት እንደተገመገመ ጠቅሰዋል፡፡ በኢትዮጵያ የቡድንና የግል ፍላጎትን በኃይል ለማሳካት ያሰቡ ጽንፈኛ አካላት ህብረ ብሔራዊ አንድነታችን እየፈተኑት ነው ያሉት አቶ አደም፤ ነፃነትን ለመጠቀም የሌሎችን ነፃነት ማክበር እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው የህግ የበላይነትንና ህገ መንግስታዊነትን ማረጋገጥ፣ የተሟላ ሀገራዊ ሰላምን ማፅናት፣ የፍትሕና ፀጥታ ተቋማትን ማጠናከር፣ የሁለም ኢትዮጵያውያን የወል እውነቶችን ገዥ ቦታ እንዲይዙ ማድረግ እንደሚገባ አቅጣጫ ማስቀመጡን ተናግረዋል። ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ባለፉት 10 ወራት ፍትሐዊ ልማትን ከማረጋገጥ አንጻር አካታች ኢኮኖሚ እየተገነባ መሆኑን በውይይቱ እንደተመለከተም አብራርተዋል። የብዝኃ ዘርፍ የኢኮኖሚ ስርዓትን በማስቀጠል የተመዘገቡ ስኬቶች መኖራቸውን ገልጸው፤ በተለይም በስንዴ ምርታማነት የታየውን ውጤት በትልቅ ስኬት ማነሳቱን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የኢንዱስትሪ ዘርፉን ችግር በመፍታት፣ ምርታማነትን ለማሳደግና የገበያ ትስስር በመፍጠር አበረታች ውጤቶች መገኘታቸውን ገልጸዋል፡፡ በገበታ ለሀገር እና ሌሎች ፕሮጀክቶች የቱሪዝም ዘርፉን ለማነቃቃት መቻሉን እንዲሁም ከስራ ዕድል ፈጠራ አኳያ በዘጠኝ ወራት ውስጥ 2 ነጥብ 4 ሚሊየን ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸው በቀጣይም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ የፓርቲው ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ የዋጋ ንረትን ለማረጋገት፣ ኮንትሮባንድን ለመከላከል፣ በአምራችና ሸማቹ መካከል እሴት የማይጨምሩ የገበያ ሰንሰለቶችን ለመቀነስ ጠንካራ ርምጃዎች እንዲወሰዱ አቅጣጫ ማስቀመጡን ተናግረዋል፡፡ በኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ አካታች የማህበራዊ ልማትን ለማጎልበት በትምህርት፣ በጤና እንዲሁም በወጣቶችና ሴቶች ተጠቃሚነት ላይ አበረታች ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም በማህበራዊ መስክ ያሉ የትምህርት ጥራት፣ ፍትሐዊነትና እኩል ተጠቃሚነትን መሰረተ ያደረገ ሥነ ምግባራዊና ሀገር ውዳድ ትውልድ ግንባታ ይከናወናል ብለዋል፡፡ ትብብርና የጋራ ተጠቃሚነትን መሰረት ባደረጉ የዲፕሎማሲ ስራዎች ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቅሰው፤ ለጎረቤት ሀገራት ቅድሚያ በመስጠት የኢኮኖሚ ትስስር ፣ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት እንዲጠናከር የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው ይቀጥላሉ ነው ያሉት። የሀገርን ክብር የማስጠበቅ አካሄዳችን ያልተመቻቸው አካላት የሰሜኑን ጦርነት ተከትሎ የፈጠሩብንን ጫና በመቋቋም የሀገር ሉዓላዊነታችንና የግዛት አንድነታችንን አስጠብቀን ቀጥለናል ብለዋል፡፡ ለአፍሪካዊ ችግር አፍሪካዊ መፍትሔ የመስጠት መርህ ውጤት በማስገኘቱ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ በቀጣይም ሚዛኑን የጠበቀ ሁሉን አቀፍ ዲፕሎማሲያዊ አካሄድን በመከተል የፖሊሲ ነጻነታችንን የሚጋፉና ፍትሐዊ ተጠቃሚነታችንን እንዳናረጋገጥ የሚፈትኑ ጫናዎችን የመመከትና ወዳጅነትን የማስፋት ስራ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አቅጣጫ መቀመጡን አንስተዋል። ብልጽግና ፓርቲ የተጀመሩ ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ዲፕሎማሲያዊ ስራዎች በስኬት እንዲቀጥሉ የፓርቲውን አመራር የማጥራት፣ የማጠናከርና የመገንባት ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡ ፈጠራና ፍጥነትን ተጠቅሞ የፓርቲውን አደረጃጀት ማጠናከር፣ የውስጠ ፓርቲ አንድነትና ዴሞክራሲን ማጎልበት፣ ብሎም በምርጫ ወቅት ለህዝብ የተገባውን ቃል በውጤታማነት መፈጸም የቀጣይ ትኩረት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ለዘላቂ ሰላም መስፈን የድርሻቸውን እንደሚወጡ የጌዴኦ ዞን የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ
May 31, 2023 103
ዲላ ግንቦት 23/2015 (ኢዜአ) ለዘላቂ ሰላም መስፈን የድርሻቸውን እንደሚወጡ የጌዴኦ ዞን የቤተ እምነት መሪዎችና የባህል አባቶች አስታወቁ። የሰላም እሴቶችን ለማጽናትና ግጭቶችን አስቀድሞ መከላከልን ዓላማው ያደረገ የሰላም እሴት ግንባታ ዙሪያ የሚመክር መድረክ ዛሬ በዲላ ከተማ ተካሂዷል።   በመድረኩ ላይ የቤተ እምነት መሪዎች፣ የባህልና የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም የጌዴኦ ዞንና የዲላ ከተማ አስተዳደር የስራ ሃላፊዎች ተሳትፈዋል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል በኢትዮጵያ የወንጌል አማኞች ሙሉ ወንጌል ቤተክርስቲያን የልማት ካውንስል ዳይሬክተር መጋቢ ቦካኮ ዱጉማ እንዳሉት ስለ ሰላም መስራት የቤተ እምነቶች ተቀዳሚ ተልዕኮ ነው። "ልጆቻችንን ስናሳደግ ጥላቻና በደል እያስተማርን ሳይሆን ለሀገርና ለወገን የሚበጀውን ስለ ፍቅር፣ ሰላም፣ አብሮነትና አንድነትን በመመገብ ሊሆን ይገባል" ብለዋል። በተለይም ታሪክን ለአገር ግንባታና ለትውልድ ትምህርት መውሰድ እንጂ የጠብና የግጭት ምንጭ አድርገን መተረክ እንደማይገባ አስገንዝበዋል። የቋንቋና የሃይማኖት ልዩነቶች ውበትና ጸጋዎች መሆናቸውን ተረድተን ከአክራሪነትና የኔ ብቻ ከሚል ጽንፈኝነት ይልቅ ለሰላምና ለመቻቻል ቅድሚያ መስጠት ይገባል ብለዋል። በተለይም በሀገራችን የመጣውን የሰላም አየር ዘላቂና ወንድማማችነትን ያጎለበተ እንዲሆን ግንባር ቀደም ሃላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል ብለዋል። የጌዴኦ ብሔር ባህላዊ የባሌ አስተዳደር መሪ አባ ገዳ ቢፎሚ ዋቆ በበኩላቸው በሀገራችን የሚገኙ በርካታ ባህሎች ለሰላም ግንባታ ጠቃሚ እሴቶች ያሉ ቢሆንም በአግባቡ ከመጠቀም አንጸር ውስንነቶች መኖራቸውን ጠቅሰዋል። የባህል አባቶችና የቤተ እምነት መሪዎች "ግጭትን ለማስቀረት የምናደርገውን ጥረት ያክል ያገኝነውን የሰላም አየር ዘላቂ ለማድረግም ልንሰራና ልንጥር ይገባል" ብለዋል። በተለይም በውስጣችን ለግጭት መነሻ የሆኑ አስተሳሰቦችን በውይይት የመፍታት ባህላችንን በማሳደግ ለትውልዱም ሆነ ለሀገራችን የፖለቲካ ስርዓቱ ምሳሌ መሆን ይጠበቅብናል ሲሉም ተናግረዋል። የሰላም እሴቶችን ማስተዋወቅና ማስተማር ለዘላቂ ሰላም መሰረት መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የጌዴኦ ዞን የሃይማኖት ተቋማት ካውንስል ሰብሳቢ ቄስ አያሌው ሙርቲ ናቸው። የተለያዩ ሃይማኖት ተከታዮች ከጥላቻና መገፋፋት ይልቅ ወንድማማችነትንና ወዳጅነትን እንዲያስቀድሙ የጋራ እሴቶች ላይ በትኩረት መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የጌዴኦ ዞን ምክር ቤት አፈጉባኤ ወይዘሮ ምስጋና ዋቀዮ በበኩላቸው በሀገራችን የመጣውን የሰላም ሁኔታ ሊያሻክሩ የሚችሉ ጽንፈኝነትን በጋራ መከላከል ይገባል ብለዋል። በተለይም በተለያዩ የሚዲያ አማራጮች ጥላቻና ግጭትን የሚሰብኩ የፖለቲካ ነጋዴዎች ተቀባይነት እንዳያገኙና ትውልዱን በሰላም እሴቶች በመገንባቱ ረገድ የቤተ እምነት መሪዎችና የባህል አባቶች ድርሻቸው የጎላ መሆኑን ጠቅሰዋል። በአንጻሩ ወንድማማችነትን የሚያጎለብቱ መድረኮችን በማጠናከር ሀገራዊ ሰላማችንን ዘላቂ በማድረጉ ረገድ የድርሻቸውን መወጣት እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል። የዲላ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ተስፋጽዮን ዳካ በበኩላቸው በህብረተሰቡ ዘንድ መግባባት እና መተማመን በመፍጠር ፍፁም የሆነ ሰላም ማምጣት እንደሚቻል አመላክተዋል። ከግጭት የሚያተርፉ አካላት መቼውንም ጊዜ ለሰላም ፍላጎት የሌላቸው በመሆኑ የጋራ ትግል ማድረግ እንደሚገባም አሳስበዋል። መሰል የሰላም ግንባታ ስራዎች ደግሞ ወጣቱን በይበልጥ ተሳታፊ ማድረግ እንዳለበት ጠቅሰው፤ በተለይ አባቶች ትክክለኛውን ታሪክ ለትውልድ በማስተላለፍ ለሰላም ግንባታ በሚደረገው ጥረት አጋዥ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርበዋል።    
የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለእጀባ ለበረራ ደህንነትና ቁልፍ የመሰረተ ልማቶችን ለመጠበቅ የሰው ኃይሉን በተከታታይ ስልጠናዎች እያበቃ መሆኑ ተገለጸ
May 31, 2023 95
አዲስ አበባ ግንቦት 23/2015(ኢዜአ)፦የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የሀገር መሪዎችን፣ ቁልፍ መሰረተ ልማቶችን ከአደጋ የመጠበቅና የበረራ ደኅንነትን የማረጋገጥ ተልዕኮውን በብቃት ለመፈጸም የሰው ኃይሉን በተከታታይ ስልጠናዎች እያበቃ መሆኑን ገለጸ። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለሪፐብሊካን ጋርድና ለአገልግሎት መስሪያ ቤቱ እጀባ ፣ለበረራ ደኅንነት መኮንኖችና አመራሮች ሲሰጥ የነበረውን ስልጠና ያጠናቀቁ ሰልጣኞችን አስመርቋል። አገልግሎቱ ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መረጃ እንዳመለከተው በትብብርና በአጋርነት አብረውት ከሚሰሩ የውጭ መረጃና ደኅንነት ተቋማት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ይህ ስልጠና በዋናነት በቪአይፒ ደኅንነት ጥበቃ፣ በፈንጂ ምህንድስና ፣በድሮን አጠቃቀም ቅየሳና የአደጋ ምላሽ አሰጣጥ ላይ ያተኮረ ነው። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ሲሳይ ቶላ በምረቃው ላይ እንደገለጹት አደጋ መቼና እንዴት እንደሚከሰት በእርግጠኝነት መናገር ባይቻልም በማያቋርጥ ስልጠናና ልምምድ ብቁና ሁሌም ዝግጁ ሆኖ መገኘት አስፈላጊ በመሆኑ አገልግሎት መስሪያ ቤቱ የዚህ አይነቱን ስልጠና አዘጋጅቷል። በመሆኑም አገልግሎት መስሪያ ቤቱ የሀገር መሪዎችን ፣ቁልፍ መሰረተ ልማቶችን ከአደጋ የመጠበቅ እንዲሁም የበረራ ደኅንነትን የማረጋገጥ ተልዕኮዎችን ለመፈጸም የሰው ኃይሉን በተከታታይ ስልጠና እንደሚያጠናክርም ተናግረዋል። ሰልጣኞችም በስልጠና ወቅት በንድፈ ሃሳብ፡ በተግባርና በቴክኖሎጂ የተደገፈ ስልጠና ማግኘታቸው ለተቋማዊ ተልዕኮ ስኬታማ አፈፃፀም ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል።   የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ፕሬዝዳንት አቶ ወንድወሰን ካሳ በበኩላቸው የቪአይፒ ደኅንነት ጥበቃ መኮንኖች ከፍተኛ ደኅንነታዊ አንድምታ ያላቸውን ግለሰቦች ደኅንነት ለመጠበቅ ተገቢውን ዕውቀት ፣ ክህሎት፣ አስተሳሰብ እና ስነምግባር ሊጨብጡ ይገባል ብለዋል። እያንዳንዱ የቪአይፒ ደኅንነት ጥበቃ ስምሪት ሊያጋጥሙ ከሚችሉ እንዲሁም ከሚገመቱና ካልተጠበቁ ስጋቶች እና ጥቃቶች የሀገር መሪዎችን፣ ቁልፍ የመሰረት ልማት ተቋማትን በብቃት ለመከላከል የሚያስችል የተሟላ ዕቅድ አዘጋጅቶ የመሰማራት ባህልን ማዳበር እንደሚገባ ገልጸዋል። በብሔራዊ የመረጃና ደኅንነት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በንድፈ-ሃሳብና በተግባር የተሰጠውን ስልጠና የተከታተሉ ሰልጣኞችም ያገኙትን ዕውቀትና ክህሎት በተግባር ልምምድ ማሳየታቸውን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት መረጃ አመልክቷል።
በኦሮሚያ ክልል ሰላምን ለማረጋገጥ ከሃይማኖት ተቋማት ጋር በቅንጅት እየተሰራ ነው--አቶ ሃይሉ አዱኛ
May 31, 2023 131
አዲስ አበባ ግንቦት 23/2015(ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል ሰላምን ለማረጋገጥ የክልሉ መንግስት ከሃይማኖት ተቋማት ጋር በቅንጅት እየሰራ መሆኑን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ ሃላፊ አቶ ሃይሉ አዱኛ ገለጹ። ሃላፊው ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት መግለጫ እንዳመለከቱት ኢትዮጵያ የተለያየ እምነት ተከታዮች ተከባብረው የሚኖሩባት እንደመሆኗ የክልሉ መንግስትም በሃይማኖት እኩልነት የሚያምንና እውቅናም የሚሰጥ ነው። አንዳንድ አካላት በኦሮሚያ ክልል ህገ ወጥ ግንባታዎችን የማፍረሱን ሥራ በአንድ ሃይማኖት ላይ ያነጣጠረ ማስመሰላቸው ፈጽሞ ትክክል አለመሆኑን አቶ ሃይሉ ተናግረዋል። በመሆኑም የሕገ-ወጥ ቤቶች ፈረሳ ሒደት መስጅድ ላይ ያተኮረ አለመሆኑንና በክልሉ 600 በሚሆኑ ከተሞች በህገ-ወጥ መንገድ የተገነቡ ቤቶችን የማፍረስ ሒደት እንደሚከናወን ገልጸዋል። ሕግ የማስከበር ስራውም በዋናነት ህገ-ወጥነትን በዘላቂነት ለመከላከል ያለመ ነው ሲሉ አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡ በቀጣይም የክልሉ መንግስት በሃይማኖት ጉዳዮች ላይ ከሃይማኖት ተቋማት ጋር በቅንጅት እንደሚሰራ በማረጋገጥ የሃይማኖት ተቋማት እና የእምነቱ ተከታዮችም እምነትን ተገን አድርገው ሁከት እና ብጥብጥ ለመፍጠር የሚሞክሩ አካላትን በጋራ እንዲከላከሉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በቻይና ያደረጉት ጉብኝት የኢትዮጵያና የቻይና ወዳጅነትና ትብብርን ከፍ ያደረገ ነው- የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
May 31, 2023 161
አዲስ አበባ ግንቦት 23/2015(ኢዜአ):-ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን በቻይና ያደረጉት ጉብኝት የኢትዮጵያና ቻይና ወዳጅነትና ትብብርን ወደ ላቀ ደረጃ ከፍ ማድረጉን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ አምባሳደር መለስ ዓለም፤ በውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ መስክ በሳምንቱ በተከናወኑ አበይት ጉዳዮች ላይ በማተኮር መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከግንቦት 15 እስከ 20 ቀን 2015 ዓ.ም በቻይና ይፉዊ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል። የጉብኝቱ አላማ የአገራቱን አገሮች የትብብር ግንኙነትና ወዳጅነት ማጠናከርን ዓላማ ያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በቻይና ጉብኝታቸው ከተለያዩ የአገሪቷ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች ጋር ሁሉን አቀፍ ውይይት ማድረጋቸውን ገልጸዋል። የኢትዮ-ቻይና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በማጠናከር በሁሉም መስክ በትብብር ለመስራት በሚያስችሉ ጉዳዮች ዙሪያ መነጋገራቸውን አምባሳደር መለስ ተናግረዋል። በቻይና የሁለቱን አገራት የንግድ ትስስር የሚያጎለብት የንግድና ኢንቨስትመንት መድረክ በጉብኝታቸው ወቅት መካሄዱንም ጠቅሰዋል። የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጉበኝት የኢትዮ-ቻይናን የሁለትዮሽና የባለብዙ ወገን ትብብር የሚያጠናክር መሆኑን አብራርተዋል። የኢትዮጵያን ታሪክና ስልጣኔ በሚመጥን መልኩ በቻይና የኢትዮጵያ ኢምባሲ በነበረበት ቦታ በአዲስ መልክ ተገንብቶ መመረቁንም ገልጸዋል። የኢትዮ ቻይና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የተጀመረው እ.አ.አ በ1970 ሲሆን በቀጣዩ ዓመትም የየአገራቱ ኢምባሲዎች በአዲስ አበባና ቤጅንግ መክፈታቸውን መረጃዎች ይጠቁማሉ። የሁለቱ አገሮች ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት እየተጠናከረ መጥቶ ከ2006 ጀምሮ ቻይና የኢትዮጵያ ዋነኛ የንግድ አጋር መሆን ችላለች። በኢንቨሰትመንት መስክም በርካታ የቻይና ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በተለያዩ የልማት መስኮች ሙአለንዋያቸውን በማፍሰስ በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ።  
ዋናውን የምክክር ሂደት በቀጣይ ዓመት ለመጀመር የሚያስችል ሥራ እየተሰራ ነው - ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ
May 31, 2023 173
ሚዛን አማን፣ ግንቦት 23 / 2015 (ኢዜአ):- አገራዊ ምክክር ኮሚሽን የተቋቋመበትን ዋናውን የምክክር ሂደት በሚቀጥለው ዓመት ለመጀመር የሚያስችል ሥራ እየተሰራ መሆኑን የኮሚሽኑ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ ገለጹ። ኮሚሽኑ ሰሞኑን በተለያዩ ክልሎች የሀገራዊ ምክክር ተሳታፊ ምልመላ ሂደት እና አጀንዳ ማሰ ባሰብ ላይ ያተኮረ ስልጠና ለተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች እየሰጠ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ሲሰጥ በነበረው ስልጠና ላይ የተገኙት የኮሚሽኑ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ ምንም አይነት አጀንዳ ወደ ኋላ እንዳይቀር በጥንቃቄ እየተመራ ነው ብለዋል። በሚቀጥለው ዓመት ወደ ምክክር ለመግባት የሚያስችሉ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆኑን ጠቅሰዋል። በሁሉም መዋቅሮች ከተለያዩ አደረጃጀቶች ተሳታፊዎችን የሚመለምሉ ሰባት ተባባሪ አካላት የተመረጡ ሲሆን ግልጽ አካታችና ተዓማኒነት ያለው እንዲሆን መልማዮች ተገቢውን ስልጠና ወስደዋል ነው ያሉት።   በሚመለመሉ ተሳታፊዎች በኩል የሚሰበሰቡ ሀገራዊ የህዝብ አጀንዳዎች ለኮሚሽኑ ምክር ቤት ደርሰው ለምክክር ይቀርባሉ በማለት ገልጸው፤ የአካባቢ አጀንዳዎች በመዋቅር ደረጃ እንዲፈቱ እናመቻቻለን ብለዋል። ሀገራዊ አጀንዳ አለኝ የሚል ማንኛውም አካል ሀሳቡ እንዳይቀርበት በአደረጃጀት በኩል ከመስጠት ባለፈ በስልክ፣ በአካልና ሌሎች የሀሳብ ማቅረቢያ መንገዶች ለኮሚሽኑ እንዲሰጥ አመቻችተን እየተቀበልን ነው ሲሉ አክለዋል። ለሀገራዊ ችግሮች መፍትሔው መወያየት መሆኑን ገልጸው፤ ለመወያየት ደግሞ በተገቢው መንገድ መደማመጥ እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። በቦንጋ ከተማ በተካሄደው የአጀንዳ አሰባሰብ እና የተሳታፊ ምልመላ ስልጠና ከወሰዱ ተባባሪ አካላት መካከል ከዳውሮ ዞን ተርጫ ከተማ የተገኙት አቶ ዳዊት ወንድሙ በሰጡት አስተያየት ለምክክሩ ስኬት የድርሻቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። ችግሮችን ለመፍታት ምንጩን ማወቅ ተገቢ በመሆኑ ህብረተሰቡ በአግባቡ አጀንዳውን ለምክክር ኮሚሽኑ ማቅረብ እንዳለበት ጠቁመዋል። ከካፋ ዞን ገዋታ ወረዳ የተገኙት መምህርት ጥሩነሽ ወንዳፍራሽ በበኩላቸው የመወያየትና ችግሮችን በጋራ የመፍታት ባህል አለን ሲሉ ገልጸዋል። ምክክሩ በዚህ አግባብ የሚፈጸም መሆኑ መግባባትን ለመፍጠር ትልቅ ዕድል እንደሆነ ተናግረዋል። ከዘር፣ ከፖለቲካና ከእምነት መሰል ተጽዕኖዎች ነጻ የሆኑ አካላት በምክክር ኮሚሽኑ ውይይት እንዲሳተፉ በጥንቃቄ የምልመላውን ሂደት እንሰራለን ብለዋል። በጥቃቅን ጉዳዮች የሚፈጠር ግጭት ያስከተለብን ጉዳት ቀላል ባለመሆኑ በምክክሩ ተነጋግረን በመግባባት ሀገራችንን ወደ ፊት ማራመድ አለብን ያሉት ደግሞ ከቤንች ሸኮ ዞን የተሳተፉት አቶ ብርሃኑ ገብረመድኅን ናቸው። በውይይት ችግሮችን የመፍታት ባህላችን መሸርሸሩ ያስከተለብንን ቀውስ አሁን እየተፈጠረ ባለው የምክክር መድረክ ለመፍታት ሁላችንም የበኩላችንን ጥረት እናደርጋለን ብለዋል።  
የመከላከያ ዋር ኮሌጅ አመራሮች እና ከፍተኛ ሰልጣኝ መኮንኖች በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉብኝት አደረጉ
May 30, 2023 142
አዲስ አበባ ግንቦት 22/2015 (ኢዜአ) ፦የመከላከያ ዋር ኮሌጅ አመራሮች እና ከፍተኛ ሰልጣኝ መኮንኖች በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ጉብኝት አድርገዋል። የምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን መልዕክት የጽህፈት ቤታቸው ኃላፊ አምባሳደር እሸቴ ጥላሁን ያቀረቡ ሲሆን፤ የአገር መከላከያ ሰራዊት በሁሉም አውዶች የአገርን ደህንነት እና ሉዓላዊነት ከጥቃት ለመጠበቅ ከሕዝብ አብራክ ወጥቶ ለሕዝብ እየኖረ ያለ የዜጎች አለኝታ በመሆኑ ላቅ ያለ ክብር የሚገባው ነው ብለዋል።   የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና መከላከያ ሰራዊት የአገር እና የሕዝብ መከታ መሆናቸውንም ገልጸዋል። የመከላከያ ዋር ኮሌጅ ዋና አዛዥ ብርጋዴር ጀኔራል ቡልቲ ታደሰ በበኩላቸው ኮሌጁ በሰው ኃይል ግንባታ ተማሪዎችን ተቀብሎ በማስተማር እና ስልጠናዎችን በመስጠት በሰው ኃይል ግንባታ ብቁ እንዲሆኑ እየሰራ መሆኑን አመልክተዋል። ሰራዊቱ በዓለም ሰላም ማስከበር እና በሌሎች ተልኮዎች ውጤታማነቱን ማስመስከሩን ገልጸው ኮሌጁ በቀጣይም ስራውን በተሻለ ተግባር እንዲከውን የሚያስችል ስልጠና እየሰጠ ነው ብለዋል ። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲቲዩት የፖለቲካ ሳይንስ መሪ ተመራማሪ የሆኑት ዶክተር ዳር እስከዳር ታዬ “የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ፖሊስ ትናንት እና ዛሬ” በሚል የመወያያ ጽሑፍ አቅርበው ውይይት ተደርጎበታል። በውይይቱ ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ መሰጠቱን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በመዲናዋ በተለያዩ አካባቢዎች ህዝብን እያማረሩ ያሉ ህገ-ወጥ ጫኝና አውራጆች ላይ ህጋዊ እርምጃ ተወስዷል- የአዲስ አበባ ሰላምና  ጸጥታ አስተዳደር  ቢሮ
May 30, 2023 144
አዲስ አበባ ግንቦት 22/2015(ኢዜአ)፡- በአዲስ አበባ በተለያዩ አካባቢዎች ህዝብን እያማረሩ ያሉ ህገ-ወጥ ጫኝና አውራጆች ላይ ህጋዊ እርምጃ መወሰዱን የአዲስ አበባ ሰላምና ጸጥታ አስተዳደር ቢሮ አስታወቀ፡፡ የቢሮው ኃላፊ ወይዘሮ ሊዲያ ግርማ ጉዳዩን አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ ፤ በከተማዋ በተለያዩ አካባቢዎች በኢ-መደበኛ መንገድ የተደራጁ ጫኝና አውራጆች ከመጠን በላይ በማስከፈል እና ለህግና ስርዓት ተገዥ ባለመሆን ህዝብን እያማረሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተለይም በጋራ መኖሪያ ቤቶች አካባቢ ችግሩ በስፋት እንደሚስተዋል ገልጸው፤ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የ44 ማህበራት አባል የሆኑ 505 ጫኝና አውራጆች በህግ እንዲጠየቁ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም በተገልጋይ ላይ ድብደባና ሌሎችም የሰብዓዊ መብት ጥሰት የፈጸሙ 97 ግለሰቦች በህግ ቁጥጥር ስር መዋላቸውን አስታውቀዋል፡፡ በቀጣይም የሚወሰደው ህጋዊ እርምጃ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ኃላፊዋ አረጋግጠዋል፡፡    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም