ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
መገናኛ ብዙሀን ብሔራዊ ጥቅምን ዋነኛ አጀንዳ አድርገው መስራት ይገባቸዋል-ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)
Aug 25, 2025 83
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 19/2017(ኢዜአ)፡- መገናኛ ብዙሀን ብሔራዊ ጥቅምን ዋነኛ አጀንዳ አድርገው መስራት እንደሚገባቸው በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለፁ። "መገናኛ ብዙሃን ለብሔራዊ ጥቅም እና ለሰላም'' በሚል መሪ ሀሳብ የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን 30ኛ ዓመት ክብረ በዓል በማስመልከት የተዘጋጀ አውደ ጥናት በባህር ዳር ከተማ ተካሂዷል። ዶክተር በቂላ ሁሪሳ በአውደ ጥናቱ ላይ ''ሚዲያ ለብሔራዊ ጥቅም'' በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጥናታዊ ጽሁፍ ላይ እንደገለጹት፤ መገናኛ ብዙሀን የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ዋነኛ አጀንዳቸው አድርገው መስራት ይገባቸዋል። እንዲሁም የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅሞች በሁለንተናዊ መንገድ ማረጋገጥ የሚያስችሉ ጉዳዮችን የአጀንዳዎች ሁሉ የበላይ አጀንዳ አድርገው መንቀሳቀስ እንዳለባቸው ነው የገለጹት። በዚህም ኢትዮጵያ ሰላሟ የተረጋገጠ፣ ከድህነት ለመውጣት የምትጥር፣ በራሷ አቅም ሉአላዊነቷንና ነፃነቷን አረጋግጣ ተከብራ የምትኖር ሀገር መሆኗን ማሳየት አለባቸው ብለዋል። የክልልም ሆነ ብሔራዊ ሚዲያዎች ከነጠላ ትርክት ወጥተው የጋራ ትርክት ግንባታ ላይ በማተኮር ኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ጥቅሟን እንድታስከብርና አሸናፊ ሆና እንድትወጣ ጠንክረው እንዲሰሩም አስገንዝበዋል። ሚዲያዎች ሀገርን ሊያሻግሩ በሚችሉ አጀንዳዎች ላይ ትኩረት አድርገው መስራት ይገባቸዋል ያሉት ደግሞ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ተስፋሁን ጎበዛይ ናቸው። በተለይ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም እንዲረጋገጥ በተደራጀና ተከታታይነት ባለው መንገድ ሁሉንም አማራጮች ተጠቅመው መስራትና ማሳወቅ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። በአሁኑ ወቅት ለአሰባሳቢ አጀንዳዎች ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህንን ፈጠራ በታከለበት መንገድ ተደራሽ ማድረግ ከሚዲያዎች ይጠበቃል ብለዋል። የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን (አሚኮ) የህዝብ ድምጽ በመሆን የተጣለበትን ሃላፊነት እየተወጣ ይገኛል ያሉት ደግሞ የኮርፖሬሽኑ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሙሉቀን ሰጥየ ናቸው። አሚኮ ከህዝብ የሚነሱ ችግሮችን ማሳየት ብቻ ሳይሆን መፍትሄ እንዲያገኙ የተለያዩ የአሰራር ስልቶችን በመተግበር እየሰራ መሆኑን አመልክተዋል። በክልሉ ሰላም፣ ልማትና መልካም አስተዳደርን የተመለከቱ ሥራዎች እንዲሁም ሁሉን አቀፍ የፖለቲካ ምህዳር እንዲሰፋ ኮርፖሬሽኑ አበክሮ እየሰራ መሆኑንም አስገንዝበዋል። ቀጣይ ሃገራዊ አንድነት በሚፈጥሩና ብሔራዊ ጥቅሞችን በሚያረጋግጡ አጀንዳዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ሥራዎች እንደሚሰሩም ነው አቶ ሙሉቀን ያሳወቁት። አሚኮ በክልሉ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሥርዓት ግንባታ ላይ አበክሮ በመስራት አሻራውን እየጣለ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የአማራ ክልል ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ አማረ ሰጤ ናቸው። በቀጣይም ኮርፖሬሽኑ የተጣሉበትን ተልዕኮ በአግባቡ እንዲወጣና የልህቀት ማዕከል እንዲሆን ህዝቡ የሚጠበቅበትን እገዛ ማድረግ እንዳለበትም አፈጉባኤው አመልክተዋል። የፌደራልና የክልል አመራሮች በተገኙበት በዚህ መድረክ ሁለት ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበው ውይይት ተካሄዶባቸው ሲሆን የአሚኮ የ30ኛ ዓመት በዓልም በተለያዩ ዝግጅቶች እየተከበረ ይገኛል።
የኮሎምቢያ ምክትል ፕሬዚዳንት ፍራንሲያ ማርኬዝ አዲስ አበባ ገቡ
Aug 25, 2025 110
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 19/2017(ኢዜአ)፦ የኮሎምቢያ ምክትል ፕሬዚዳንት ፍራንሲያ ማርኬዝ ለይፋዊ የሥራ ጉብኝት አዲስ አበባ ገቡ። ምክትል ፕሬዚዳንቷ ቦሌ ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ የጤና ሚኒስትር ዶክተር መቅደስ ዳባ እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴዔታ አምባሳደር ብርሃኑ ጸጋዬ አቀባበል አድርገውላቸዋል። ምክትል ፕሬዚዳንቷ በቆይታቸው ከኢትዮጵያ መንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች ጋር የሁለቱ አገራት ግንኙነት ይበልጥ በሚጠናከርባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። ኢትዮጵያና ኮሎምቢያ በ2015 ዓ.ም በፖለቲካ ምክክርና በሌሎች የትብብር መስኮች በጋራ ለመስራት የመግባቢያ ስምምነት መፈራረማቸው ይታወቃል። ሁለቱ ሀገራት ይፋዊ የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የጀመሩት እ.አ.አ በ1947 መሆኑን መረጃዎች ያሳያሉ።
የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር ውስጣዊ አንድነትና ኢኮኖሚያዊ አቅምን ማጠናከር ይገባል
Aug 25, 2025 170
ባህርዳር ፤ ነሐሴ 19/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር ውስጣዊ አንድነትንና ኢኮኖሚያዊ አቅምን ማጠናከር እንደሚገባ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ገለፁ። የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽ(አሚኮ) 30ኛ ዓመት የምስረታ በዓልን አስመልክቶ "መገናኛ ብዙሃን ለብሄራዊ ጥቅምና ለሰላም'' በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀ አውደ ጥናት በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማዕከል አስተባባሪ ሚኒስትር ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) "ሚዲያ ለብሔራዊ ጥቅም" በሚል ርዕስ በአውደ ጥናቱ ላይ ጥናታዊ ጽሁፍ አቅርበዋል። በዚህ ጽሁፋቸው እንዳመለከቱት፤ መላው ኢትዮጵያዊ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም በሁለንተናዊ መንገድ ለማስከበር በአንድነት ሊረባረብ ይገባል። የሀገሪቱን ብሄራዊ ጥቅም የሚጎዳ ማንኛውንም እንቅስቃሴ በሀሳብ የበላይነት መሞገትና ማክሸፍም እንደሚገባ ገልጸዋል። ለዚህም ውስጣዊ አንድነትና ሰላምን በማስጠበቅ እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ አቅምን ማጠናከርና የዲሞክራሲ አቅም በመገንባት መረባረብ እንደሚገባ አብራርተዋል። መንግስት የኢትዮጵያን ብልፅግና በሁለንተናዊ መንገድ ለማረጋገጥ በሁሉም መስክ አበክሮ እየሰራ እንደሚገኝ አንስተዋል። በመሆኑም መገናኛ ብዙሀን የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ማስከበር ላይ አጀንዳ ፈጥረው መስራት እንዳለባቸው አሳስበዋል። በአውደ ጥናቱ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ፣ የአማራ ክልል ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ አማረ ሰጤን ጨምሮ ሌሎችም የስራ ሀላፊዎች እየተሳተፉ ሲሆን፤ በቀረቡ ጥናታዊ ጽሁፎች ላይ ውይይት እየተደረገ ይገኛል።
ለዕቅዱ ስኬታማነት አመራሩ በትጋትና በጥበብ መስራት አለበት-ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Aug 24, 2025 187
ባህር ዳር ፤ ነሐሴ 18/2017(ኢዜአ)፡-የክልሉን የአምስት ዓመት አሻጋሪ ዕቅድ ስኬታማ ለማድረግ አመራሩ ጠንካራ የልማት ትግል ማድረግ እና በትጋትና በጥበብ መስራት እንዳለበት የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ አሳሰቡ። "አርቆ ማየት፤ አልቆ መስራት ለህዝባችን ከፍታ'' በሚል መሪ ሀሳብ በክልሉ የ25 ዓመት የአሻጋሪ እድገትና ዘላቂ ልማት ፍኖተ ካርታ እንዲሁም የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ላይ ያተኮረ ውይይት በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። ርዕሰ መስተዳድሩ አረጋ ከበደ በመድረኩ እንደገለጹት፣ ስትራቴጂክ ዕቅዱ በክልሉ ያለውን ፀጋ በመጠቀም የህዝቡን የልማት ተጠቃሚነትና የክልሉን እድገት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የሚያስችል ነው። ክልሉ አሁን ያለበትን ተጨባጭ ሁኔታ በጥልቀት ከማመላከት ባለፈ በክልሉ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ሰላም ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት የሚፈጠርበት መሆኑን አመልክተዋል። ዕቅዱ በትውልዶች ቅብብል የሚተገበር ነው ያሉት አቶ አረጋ፣ ቀጣይና ተከታታይ በሆነ መንገድ ተደማሪ ውጤት በሚያስመዘግብ አግባብ የሚተገበር መሆኑንም አስረድተዋል። በተለይ በዚህ ዓመት የተፈለገውን ውጤት ለማምጣት የይቻላል መንፈስን በሚፈጥር መንገድ መተግበር ዋነኛ ትኩረታችን መሆን አለበት ሲሉም ነው ያሳሰቡት። በዕቅዱ ላይ ህዝብን በባለቤትነት ለማሳተፍ ውይይት መደረጉን የገለጹት ርዕሰ መስተዳድሩ፣ በዚህም ህዝቡ ተስፋ ማድረጉንና ተስፋውን እውን ለማድረግ አመራሩ በቁጭትና በትጋት ሊሰራ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ችግር ቀልባሽና አሻጋሪ ሆኖ የተዘጋጀውን ዕቅድ ስኬታማ ለማድረግ እምቅ የአመራር ጥበብን መጠቀምና በጥበብና በትጋት መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል። ለዚህም አመራሩ ከልማዳዊ አሰራር ወጥቶ ሥራውን በላቀ ትጋት በማከናወን የህዝብን የልማት እርካታ ማረጋገጥ አለበት ሲሉም ነው ያስገነዘቡት። የበለፀገ ህዝብና ክልል ለመገንባት ከተናጠል ጥረት ይልቅ የጋራ ትጋት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ሀላፊ ደመቀ ቦሩ (ዶ/ር) ናቸው። የክልሉ የ25 ዓመት የአሻጋሪ እድገትና የዘላቂ ልማት ፍኖተ ካርታ እንዲሁም የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ዕቅድ ሁለንተናዊ ብልጽግናን በሚያሳካ አግባብ ተነድፎ ወደ ትግበራ መገባቱን አንስተዋል። ዕቅዱ የህዝብ መሆኑን ጠቁመው፣ አመራሩ ጠንካራ ተቋማትን በመገንባት በላቀ ቁርጠኝነትና መግባባት እውን ሊያደርገው እንደሚገባ ገልፀዋል። መድረኩ ከዛሬ ጀምሮ እስከ ነሐሴ 26 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ የሚቆይ ሲሆን የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ በየደረጃው ያሉ አመራሮችም በመሳተፍ ላይ ናቸው።
ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ እርሾ የሆኑ ሀገራዊ እሴቶች ወደ ገበያው መምጣት አለባቸው - ሙዓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት
Aug 24, 2025 217
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 18/2017(ኢዜአ)፡-ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ እርሾ የሆኑ ሀገራዊ እሴቶች ወደ ገበያው መምጣት እንዳለባቸው የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ ሚኒስትር ሙዓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ገለጹ፡፡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) “ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲ ፍለጋ” በሚል ርዕስ ተጽፎ ለአንባብያን በደረሰው መጽሀፍ ዙሪያ በተለያዩ የሥራ መስኮች የሚገኙ ባለሙያዎች እና ከፍተኛ ሥራ ኃላፊዎች ውይይት አድርገውበታል፡፡ የጋዜጠኝነት እና ስነ ተግባቦት ባለሙያ እና ተመራማሪ አቶ ከማል ሀሺ በበኩላቸው፥ በተለይ ከለውጡ በኋላ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አርአያነትን በመከተል ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ኃላፊዎች ያካበቱትን ልምድ እና እውቀት በመጽሀፍ መልኩ ለሕዝቡ ማካፈላቸው የሚያስመሰግን ልምምድ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) "ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲ" ፍለጋ በሚል ርዕስ በቅርቡ ያሳተሙት መጽሀፍ ከፍተኛ የምርምር ሥራዎች የታዩበት እና ለምንፈልገው ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲ ታላቅ አበርክቶ ያለው ስለመሆኑ አብራርተዋል፡፡ የፍልስፍና ምሁር እና ተመራማሪ አቶ ዘሪሁን ተሾመ፥ ከሌሎች አገሮች በመቅዳት ዴሞክራሲን ኢትዮጵያ ውስጥ ለመተግበር የተደረጉ ጥረቶች ውጤት እንዳላመጡ ያብራራሉ፡፡ በዚህ ረገድ "ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲ ፍለጋ" በሚል ርዕስ የተጻፈው የተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) መጽሀፍ ለሀገር በቀል እውቀት ትኩረት በመስጠት ኢትዮጵያን የሚመስል ዴሞክራሲ ለመገንባት የሚያስችል ጥረት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ ሚኒስትር ሙዓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ይህን ሀሳብ ያጠናክራሉ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በተለያዩ የሀገሪቷ አካባቢዎች የሚገኙ የሽምግልና፣ የእርቅ፣ የሕግ እና ሌሎች ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ የሚጠቅሙ እሴቶች እንዲታወቁ የማድረጉ ስራ መቀጠል እንዳለበት ተናግረዋል፡፡
“ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲ ፍለጋ” መጽሀፍ ለኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ግንባታ ቁልፍ ሚና ሊጫወት ይችላል
Aug 24, 2025 205
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 18/2017(ኢዜአ)፡-“ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲ ፍለጋ” በሚል ርዕስ ለሕትመት የበቃው የተስፋዬ በልጂጌ (ዶ/ር) መጽሀፍ ለኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ግንባታ ቁልፍ ሚና ሊጫወት እንደሚችል ተገለጸ፡፡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ተጽፎ ለአንባብያን የደረሰው መጽሀፍ ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ግንባታ ትልቅ ፋይዳ እንደሚኖረው ተገልጿል፡፡ መጽሀፉን በተመለከተ በተለያዩ የስራ መስኮች የሚገኙ ባለሙያዎች እና ባለስልጣናት ውይይት አድርገውበታል፡፡ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ ሚኒስትር ሙዓዘ ጥበባት ዲያቆን ዳንኤል ክብረት ባወያዩት መድረክ መጽሀፉ ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ግንባታ ያለው አስተዋጽኦ በስፋት ተዳሷል፡፡ በመድረኩ ላይ ሀሳባቸውን ያካፈሉት የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ከይረዲን ተዘራ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ በመጽሀፉ ኢትዮጵያ ለዴሞክራሲ ግንባታ እርሾ የሚሆን የዳበረ ማህበራዊ እና አስተዳደራዊ እሴት አላት። ሌላው በውይይቱ የተሳተፉት አንጋፋው ፖለቲከኛ አምባሳደር ሌንጮ ባቲ በሰጡት አስተያየት ዴሞክራሲ በኢትዮጵያ በርካታ ዓመታትን ያስቆጠረ የሕዝብ ጥያቄ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በኢትዮጵያ ዴሞክራሲ ሲነሳ ከሀገረ መንግስቱ ጋር ተጣምሮ የሚነሳ በመሆኑ የዴሞክራሲ ግንባታ ጉዞውን እንዳወሳሰበው ገልጸዋል፡፡ መጽሀፉ ይህን የዘመናት የዴሞክራሲ ጥያቄ ከኢትዮጵያዊ ፍልስፍና ጋር አገናኝቶ ማምጣቱ የሚደነቅ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያን የመሰለ ጥንታዊት እና የዳበረ ባህላዊ ስርዓት ያላተ ሀገር ዴሞክራሲን መገንባት እንቆቅልሽ ያደረገው ምስጢር እንቅልፍ እንደሚነሳቸው የተናገሩት ተስፋዬ በልጂጌ (ዶ/ር)፤ ይህ ቁጭት “ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲ ፍለጋ” የሚለውን መጽሀፍ እንዲጽፉ እንዳነሳሳቸው ገልጸዋል፡፡ መጽሀፋ ወደፊት ለኢትዮጵያ የሚበጅ ዴሞክራሲን በመገንባት ሂደት መነሻ ሀሳብ ሆኖ እንደሚያገለግል ያላቸውን እምነት ገልጸዋል፡፡
በክልሉ የህዝብን የላቀ የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ አመራሩ በቁጭት ሊሰራ ይገባል-ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Aug 24, 2025 216
ባህር ዳር፤ ነሐሴ 18/2017(ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የህዝብን የላቀ የልማት ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና ብልፅግናን እውን ለማድረግ በየደረጃው ያለው አመራር በቁጭት መስራት እንዳለበት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። ''አርቆ ማየት፤ አልቆ መስራት ለህዝባችን ከፍታ'' በሚል መሪ ሀሳብ የአመራር ውይይት በባህር ዳር ከተማ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል። መድረኩ የክልሉን የ25 ዓመት አሻጋሪ የልማት ፍኖተ ካርታ እና የአምስት ዓመት ስትራቴጅክ ዕቅድ ላይ ያተኮረ መሆኑም ተመላክቷል። በመድረኩ ላይ የተገኙት ርዕስ መስተዳድር አረጋ ከበደ እንደገለጹት ክልሉን አሁን ካለበት ተግዳሮት በማላቀቅ ህዝቡን በየደረጃው ተጠቃሚ የሚያደርግ እድገት ማስመዝገብ ይገባል። ለዚህም የሚገጥሙ ወቅታዊ ችግሮችን በላቀ አመራር ሰጭነትና ጥበብ በመሻገር የክልሉን ህዝብ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ተጠቃሚነቱን ለማላቅ በትኩረት እንደሚሰራ ተናግረዋል። ለእዚህም የአጭርና የረጅም ጊዜ ዕቅድ ተይዞ ወደ ተግባር መገባቱን ጠቁመው ለስኬታማነቱም በየደረጃው ያለው አመራር በቁጭት ተግቶ ሊሰራ እንደሚገባ አሳስበዋል። የክልሉ ፕላንና ልማት ቢሮ ሀላፊ ደመቀ ቦሩ (ዶ/ር) በበኩላቸው የበለፀገ ህዝብና ክልል ለመገንባት የሚከናወኑ የልማት ሥራዎች ስኬታማ እንዲሆን የልማት ዕቅዶችን በተባበረ ክንድ ማከናወን ይገባል ብለዋል። ለዚህም አሻጋሪ የሆነ የረጅም ጊዜ ዕቅድ ተነድፎ ወደ ትግበራ መገባቱን የገለጹት ሃላፊው፣ ለስኬታማነቱ ህዝቡን በነቂስ በማሳተፍ መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል። ከዛሬ ጀምሮ እስከ ነሐሴ 26 ቀን 2017 በሚቆየው በዚህ መድረክ ላይ የክልሉ አመራሮችን ጨምሮ በየደረጃው ያሉ ከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች እየተሳተፋ መሆናቸው ታውቋል።
የወታደር ውሎ አዳር መጽሐፍ መጪው ትውልድ የሠራዊቱን ጀግንነት በውል እንዲረዳ ያደርጋል
Aug 23, 2025 329
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 17/2017(ኢዜአ)፡- የወታደር ውሎ አዳር መጽሐፍ መጪው ትውልድ የሠራዊቱን ጀግንነት በውል እንዲረዳ የሚያደርግ መሆኑን የመከላከያ ጤና ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጀነራል ጥጋቡ ይልማ ገለጹ፡፡ በሌተናል ኮሎኔል ፈይሳ ናኔቻ የተጻፈው "የወታደር ውሎ አዳር" የተሰኘው መጽሐፍ በዓድዋ ድል መታሰቢያ ተመርቋል። በ23 ምዕራፎች የተከፋፈለው ይህ መፅሐፍ ለሠራዊት የስነ-ልቦና ግንባታ ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ የመከላከያ ጤና ዋና መምሪያ ኃላፊ ሌተናል ጀነራል ጥጋቡ ይልማ በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ የወታደር ውሎ አዳር መጽሐፍ ሠራዊቱ ከማሰልጠኛ ጀምሮ ያለውን እውነተኛ ህይወት የሚያስቃኝ ነው ብለዋል፡፡ ሠራዊቱ በደሙ የሚያስጠብቀውን የሀገር ሉዓላዊነትና የሚፈጽማቸውን ጀብዶች ሰንዶ ለመጪው ትውልድ ከማስተላለፍ አንጻር ደራሲው ስኬታማ ስራ መስራቱን ተናግረዋል፡፡ መጪው ትውልድ መሰል መጽሐፎችን በማንበብና ታሪክን በመረዳት የኢትዮጵያን የከፍታ ጉዞ ይበልጥ ማጽናት እንደሚጠበቅበትም ጠቁመዋል፡፡ የወታደር ውሎ አዳር መጽሐፍ ደራሲ ሌተናል ኮሎኔል ፈይሳ ናኔቻ፥ መጽሐፉ የሠራዊቱን ህይወት የሚያስቃኝና ጥንካሬውን የሚያጎለብት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ለሠራዊቱ የስነ-ልቦና ግንባታ ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑን ጠቁመው ሠራዊቱ የሀገር ሉዓላዊነት የማስጠበቅ ስራውን አጠናክሮ እንዲቀጥል የሞራል ስንቅ እንደሚሆነውም አንስተዋል፡፡ በመከላከያ የስነልቦና ግንባታ ዋና መምሪያ የሚዲያ ሥራዎች ዳይሬክተር ብርጋዴር ጀነራል አስፋው ማመጫ፤ የወታደር ውሎ አዳር መጽሐፍ የሠራዊቱን እውነተኛ መልክ የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡ ደራሲው በመጽሐፉ ሀገርን መውደድና ማክበርን በጉልህ ያስቃኘ መሆኑን ጠቁመው ሠራዊቱ ያሳለፈውን የውትድርና ህይወት የሚያሳይ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ በመጽሐፉ ምረቃ ላይ የተገኙት ሻለቃ አስቻለው ኛኙኬ እና ሻለቃ ስንታየሁ ለማ፤ መፅሐፉ ሠራዊቱ የሀገርን ሉዓላዊነትና የህዝብን ሰላም በማረጋገጥ ረገድ የሚከፍለውን የጀግንነት ዋጋ የሚያሳይ ነው ብለዋል፡፡ ከሠራዊት ግንባታ አንጻር የሚሰጠው ጠቀሜታም ጉልህ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በመፅሐፉ የምረቃ መርሐ ግብር ላይ ጀነራል መኮንኖች፣ የሠራዊቱ ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ የሠራዊት አባላት እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ታድመዋል።
ብሔራዊ ጥቅማችንን ለማስጠበቅ የተቋማት ግንባታን ማጠናከር ይገባል - ብልጽግና ፓርቲ
Aug 23, 2025 249
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 17/2017(ኢዜአ)፡- ብሔራዊ ጥቅማችንን ለማስጠበቅ የተቋማት ግንባታን ማጠናከር ይገባል ሲል የብልጽግና ፓርቲ ገለጸ። "ወደ ተምሳሌት አገር በተሻገር ሕልም፤ በላቀ ትጋት አስተማማኝ ስራ መስራት" በሚል መሪ ቃል ለአራት ተከታታይ ቀናት ሲካሄድ የነበረው የፌዴራል ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች ስልጠና መድረክ ተጠናቋል፡፡ ፓርቲው የስልጠና ማጠቃለያውን በተመለከተ ለኢዜአ በላከው መልዕክት ብሔራዊ ጥቅማችንን ለማስጠበቅ የተቋማት ግንባታን ማጠናከር ይገባል ብሏል። የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት እና የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ አደም ፋራህ እንደገለጹት ብሔራዊ ጥቅምን ለማስጠበቅ የተቋማት ግንባታ ማጠናከር ይገባል ነው ያሉት፡፡ በሁሉም ተቋማት የአገልግሎት ልህቀት ማረጋገጥ የሚያስችል ስራ መስራት እንደሚገባም ገልጸዋል፡፡ ብሔራዊ ጥቅምን ለማሳካት ከሌሎች አካላት ጋር የሚኖረውን ግንኙነት ሚዛናዊ እይታና ተራማጅ መሆን እንደሚገባም አስገንዝበዋል፡፡ አካታች ተቋማትን በመገንባትና ሲቪል የሪፎርም ስራዎችን በማጠናከር የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ በባለቤትነት መንፈስ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ የውስጠ ፓርቲ አንድነት፣ ጥንካሬና ጥራት ማረጋገጥ ከፋፋይና ሰርጎገብ አጀንዳዎችን መታገል እንደሚገባም ገልጸዋል፡፡ አመራሩ የብልጽግና እሴቶችን በመላበስ ለሕዝብ የገባናቸው ቃሎች በተግባር በመፈጸም ውጤታማነትን ማረጋገጥ ይገባል ሲሉም ተናግረዋል፡፡ አስተሳሳሪና ገዥ ትርክትን በመጠቀም በየተቋሙ ያሉ ውስጣዊ ችግሮችን በመፈተሽና በእቅድ በመምራት ሃላፊነትን በአርአያነት መወጣት እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡
በአካባቢያችን የተዋቀረው የቀበሌ አደረጃጀት በአስተዳደር እና በልማት ስራዎች የቅርብ እገዛ እያደረገልን ነው -- የምዕራብ ሸዋ ዞን ነዋሪዎች
Aug 22, 2025 323
አምቦ፤ ነሐሴ 16/2017(ኢዜአ)፡- በአካባቢያቸው የተዋቀረው የቀበሌ አደረጃጀት በአስተዳደር እና በልማት ስራዎች የቅርብ እገዛ እያደረገላቸው መሆኑን የምዕራብ ሸዋ ዞን ዳኖ ወረዳ ነዋሪዎች ገለጹ። ኢዜአ ያነጋገራቸው በምዕራብ ሸዋ ዞን በዳኖ ወረዳ የዳኖ ሸነኒ ቀበሌ ነዋሪዎች እንዳሉት፥ አዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት በአስተዳደር እና በልማት ስራዎች እያገዛቸው ነው። በወረዳው የዳኖ ሸነኒ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ጀማል ጅብሪል፤ በአካባቢያቸው በአዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት የሚፈልጉትን የመንግስት አገልግሎት በቅርበት እና በአንድ ቦታ እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ጊዜ፣ ገንዘብና ጉልበታቸውን መቆጠብ በመቻሉ ትኩረታቸው የልማት ስራ ላይ እንዲሆን እድል መፍጠሩን ጠቅሰው በአስተዳደሩ አማካኝነት የልማት ስራቸውን ለማሳደግ የሚያግዙ ግብዓቶችን በአግባቡ እያገኙ መሆኑንም አውስተዋል። የቀበሌ አደረጃጀቱ በተለይም ህዝቡና የጸጥታ አካሉ ተቀናጅተው በአካባቢው የተገኘውን ሰላም ዘላቂ ለማድረግ እገዛ ማደረጉንም ተናግረዋል። ሌላው የዚሁ ቀበሌ ነዋሪ አቶ ገመቹ አማና በበኩላቸው፣ ከዚህ በፊት አገልግሎት ለማግኘት ወደ ወረዳ በመሄድ ለተለያየ ወጪ ይጋለጡ እንደነበር አስታውሰዋል። ከአንድ ዓመት ወዲህ ግን በአካባቢው የቀበሌ አስተዳደር መዋቅር በመዘርጋቱ የመሰረተ ልማት ጥያቄዎቻቸው ምላሽ እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። አዲሱ የቀበሌ አስተዳደር መንግስታዊ አገልግሎቶችን በአንድ ቦታ እና በቅርበት ማገኘታቸው ገልጸው ለዚህም መንግስት ሊመሰገን ይገባል ያሉት ደግሞ ሌላው የቀበሌው ነዋሪ አቶ ፋዬራ አዱኛ ናቸው፡፡ በዞኑ የዳኖ ሸነኒ ቀበሌ አስተዳዳሪ አቶ ግርማ ለማ፤ አደረጃጀቱ የሕብረተሰቡን አኗኗር ለመቀየርና የልማት ጥያቄያቸው ፈጣን ምላሽ እንዲያገኝ ዓላማ አድርጎ መቋቋውን አታውሰዋል። አዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት ከተዘረጋ በኋላም የህዝቡን የአገልግሎት አሰጣጥ ተደራሽ እና ቀልጣፋ ለማድረግ የተለያዩ ጥረቶች ሲደረጉ መቆየታቸውን ገልጸዋል። ከአስተዳደራዊ ጉዳዮች ጎን ለጎን የህዝቡ የልማት ጥያቄዎች ፈጣን ምላሽ እንዲያገኙ በተለይም ከግብርና ግብዓት አቅርቦት አንጻር ውጤታማ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል።
የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በሰሜን አሜሪካ እና ካናዳ የአጀንዳ ማሰባሰብና የተወካዮች ምርጫ በቅርቡ ያካሂዳል
Aug 22, 2025 296
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 16/2017(ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በሰሜን አሜሪካ እና ካናዳ የአጀንዳ ማሰባሰብና የተወካዮች ምርጫን በቅርቡ ለማካሄድ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ገለጸ። ኮሚሽኑ እያከናወናቸው የሚገኙ ተግባራትን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥቷል። የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ቃል አቀባይ ጥበቡ ታደሰ በሰጡት መግለጫ፥ ኮሚሽኑ አካታችነትና አሳታፊነቱን በተግባር እያረጋገጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል። በዚህም ከሀገር ውጪ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን፣ ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ ተቋማት እና ማህበራትን በማሣተፍ ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በዚህም በቅርቡ በሰሜን አሜሪካ እና በካናዳ የአጀንዳ ማሰባሰብና የተወካዮች ምርጫ ለማካሄድ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በዚህ ሂደትም ኢትዮጵያውያን፣ ትውልደ ኢትዮጵያውያን፣ ተቋማት እና ማህበራት እንደሚሳተፉ ጠቁመዋል። ኮሚሽኑ ዳያስፖራ ወገኖችን በአካል እና በበይነ መረብ እንዲሳተፉ ሁኔታዎችን እንደሚያመቻችም ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅትም ለመሰብሰቢያ አዳራሽ እና ለሎጂስቲክስ ዝግጅት ይመች ዘንድ የምዝገባ ሂደት እየተከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በሰሜን አሜሪካ የሚካሄደው የአጀንዳ ማሰባሰብ እና የተወካዮች ምርጫ ነሐሴ 24 ቀን 2017 ዓ.ም እንደሚከናወን ጠቁመው፤ የካናዳውም የሰሜን አሜሪካውን ተከትሎ እንደሚካሄድ አስታውቀዋል። ሂደቱ ውጤታማ እንዲሆንም ሁሉም አካላት የነቃ ተሣትፎ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል። በህግ-ጥላ ስር የሚገኙ ዜጎችን በሀገራዊ ምክክሩ ለማሣተፍ ከፍትህ ሚኒስቴር እና ከፌዴራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር በጎ ምላሽ ተገኝቶ ለማካሄድ ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝም ገልጸዋል። ኮሚሽኑ በደቡብ አፍሪካ ያካሄደው የምክክር ሂደት በሁሉም መስኩ ውጤታማ እንደነበር አስታውሰዋል።
በዞኑ የሰፈነው ሰላም ዘላቂ እንዲሆን የህዝቡ እና የጸጥታ አካላት ጥምረት ተጠናክሮ ቀጥሏል
Aug 21, 2025 307
ነቀምቴ ፤ነሐሴ 15/2017(ኢዜአ)፡- በምስራቅ ወለጋ ዞን የሰፈነው ሰላም ዘላቂ እንዲሆን የህዝቡ እና የጸጥታ አካላት ጥምረት ተጠናክሮ መቀጠሉ ተገለጸ። ''ሰላም የልማት እና ብልጽግና መሰረት ነው'' በሚል መሪ ሀሳብ በዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተሳተፉበት የሰላም ኮንፍረንስ እየተካሄደ ነው። በዞኑ በጉቶ ጊዳ ወረዳ በተካሄደው ውይይት ላይ የተሳተፉ ነዋሪዎች በሰጡት አስተያየት በዞኑ ባለፉት ዓመታት አጋጥሞ በነበረው የጸጥታ ችግር ኢኮኖሚያዊ እና ማህበራዊ እንቅስቃሴዎች ተስተጓጉለው መቆየታቸውን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት ግን በወረዳው ሰላም በመስፈኑ ሁሉም በልማት ስራ ላይ ማተኮሩን ጠቅሰው የሰፈነው ሰላም ዘላቂ እንዲሆን ከጸጥታ አካላት ጋር ተቀናጅተው እየሰሩ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በሰላም ኮንፍረንሱ ላይ የተገኙት የወረዳው አስተዳዳሪ አቶ ተመስገን ገቢሳ፣ በወረዳው ህብረተሰቡ ከጸጥታ አካላት ጋር ተቀናጅቶ በመስራቱ አስተማማኝ ሰላም መስፈኑን ገልጸዋል። የወረዳው ነዋሪዎችም ፊታቸውን በሙሉ አቅም በልማት ስራ ላይ መሰማረራት መቻላቸውን ጠቅሰው የወረዳው አስተዳዳርም የነዋሪውን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ ስራዎችን እየፈጸመ ይገኛል ብለዋል። የምስራቅ ወለጋ ዞን አስተዳደር እና ፀጥታ ፅህፈት ቤት ሀላፊ ኮለኔል ለሜሳ ኦልጂራ በበኩላቸው ህብረተሰቡ ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ባደረገው አስተዋጽኦ ውጤት መገኘቱን አውስተዋል። አሁንም በዞኑ የበለጠ ሰላም እንዲሰፍንና የልማት ስራዎች እንዲሳልጡ ህብረተሰቡ ጸረ ሰላም ሀይሎችን ለህግ አካላት አሳልፎ በመስጠት ረገድ አስተዋጽውን ማጠናከር እንዳለበት አሳስበዋል። በዞኑ እስከ ቀበሌ ድረስ አስተማማኝ ሰላም እንዲሰፍን የህግ ማስከበር ስራው በተደራጀ መልኩ መቀጠሉን የገለጹት ደግሞ በሀገር መከላከያ ሰራዊት የ101ኛ ኮር የሎጂስቲክ ሀላፊ ኮሎኔል ኢያሱ ሀብቱ ናቸው። በዞኑ ለተገኘው ሰላም የህብረተሰቡ አስተዋጽኦ ትልቅ እንደሆነ ያስታወሱት ኮለኔሉ የዞኑ ህዝብ የሚያደርገውን ተሳትፎ ማጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል።
ኢጋድ እና ጃፓን ወጣቶችን በማብቃት፣ ሰላም እና መረጋጋት ላይ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር ተስማሙ
Aug 21, 2025 270
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 15/2017 (ኢዜአ)፡- የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን(ኢጋድ) እና ጃፓን ወጣቶችን በማብቃት፣ ሰላም እና መረጋጋት ላይ ያላቸውን ትብብር ለማጠናከር ተስማምተዋል። በጃፓን ዮካሃማ ከተማ እየተካሄደ የሚገኘው ዘጠነኛው የጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም(ቲካድ) ዛሬ ሁለተኛ ቀኑን ይዟል። የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ(ዶ/ር) ከፎረሙ ጎን ለጎን ከተለያዩ ሀገራት እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ከፍተኛ አመራሮች ጋር የሁለትዮሽ ውይይቶችን እያካሄዱ ይገኛሉ። ዋና ፀሐፊው ከጃፓን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ፉጂ ሂሳዩኪ ጋር ምክክር አድርገዋል። በውይይቱ ሁለቱ ወገኖች በዜጎች ደህንነት ጥበቃ፣ ወጣቶችን ማብቃት፣ ሰላም እና መረጋጋት ላይ ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር ተስማምተዋል። ዋና ፀሐፊው ጃፓን በሴቶች ጉዳይ፣ በሰላምና ደህንነት እንዲሁም ለኢጋድ የአመራር አካዳሚ እያደረገች ላለው ጠንካራ ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። ኢጋድ እና ጃፓን የሁለትዮሽ ትብብራቸውን የሚያጠናክር ስምምነት እ.አ.አ በ2016 መፈራረማቸውን ኢዜአ ከቀጣናዊ ተቋሙ ያገኘው መረጃ ያመለክታል። ዘጠነኛው የጃፓን አፍሪካ ልማት ዓለም አቀፍ ፎረም(ቲካድ) ነገ ይጠናቀቃል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ስለ አራቱ የመደመር ቅጾች ምን አሉ?
Aug 21, 2025 352
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ያሰናዱት አራተኛው ቅጽ የመደመር መንግሥት መጽሐፍ በቀረበበት አግባብ ልክ በሀገርም ሆነ በአፍሪካ ደረጃ ፈር ቀዳጅ መሆኑን ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የመደመር መንግሥት መጽሐፍን አስመልክቶ ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ ስለ አራቱም ቅጾች ገለጻ አድርገዋል። በገለጻቸውም ካነሷቸው ዋና ዋና ነጥቦች መካከል፡- የመጀመሪያው ቅጽ መደመር የሚለው መጽሐፍ፤ ለመደመር አጠቃላይ እሳቤ መሠረት የሚጥል ነው። የመደመር ጽንሰ ሐሳብ ንድፈ ሐሳባዊ መሠረቱ የተቀመጠው በመጀመሪያው ቅጽ ላይ ነው። የመጀመሪያው ቅጽ ከሚያነሳቸው ወሳኝ ጥያቄዎች መካከል፤ የሰው ልጅ ፍላጎት ምን ይመስላል፣ ፍላጎቱን ለማሟላት በምን መንገድ ነው ሊራመድ የሚገባው የሚሉት ይጠቀሳሉ። እነዚህን ከሰው ጋር በማስተሳሰር መጽሐፉ በዝርዝር ያነሳል። በተጨማሪም ራሱ መደመር እንደ እሳቤ ምን ማለት ነው? የሚለውን በብዙ መገለጫዎች ያመላክታል። መደመር ዓለምን እንዴት ይመለከታል? ስለ ዓለም ያለው ምልከታ በኢኮኖሚው፣ በፖለቲካው እና በዲፕሎማሲው ረገድ ምን ይመስላል? የሚለውም በመጀመሪዯው ቅጽ በዝርዝር አለ። በአጠቃላይ ቅጽ አንድ (መደመር) ሀገራዊ ጉዳዮቹን በፍልስፍና መነጽር ያስቀመጠ ሐሳብ ነው። ፍልስፍናዊ በሆነ መንገድ ያሉትን ችግሮች የሚተነትን ለእነዚያ ችግሮችም መልስ የሚያመላክት ነው። እንደ መደመር ያለ እሳቤ ለኢትዮጵያ አስፈላጊነቱ ምን እንደሆነም በዝርዝር አንስቷል። ሁለተኛው ቅጽ የሆነው የመደመር መንገድ የተነሱትን ጉዳዮች ደግሞ ሐሳብ፣ ታሪክ፣ ስትራቴጂ በሚሉ ሦስት ዋና ዋና ጉዳዮች ከፍሎ ማየት እንደሚገባ ጠቅሰዋል። በመደመር መንገድ ለይተን ካስቀመጥናቸው ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ አንዱ በወቅቱ የገጠሙንን ችግሮች በአራት የከፈልንበት ነው። እነሱም የለውጡ ሂደት የመደፈቅ አደጋ ያጋጠመበት፣ የለውጡን ሂደት ጥገናዊ ማድረግ፣ ለውጡን የተቀበሉ በመምሰል ለመጥለፍ የሞከሩ እና ለውጡ ሐቀኛ ሆኖ የሚጠበቀውን ውጤት እንዲያመጣ ማስቻል የሚሉት ናቸው። በለውጡ ጊዜ የተከተልነውን መንገድ ሊቀለብሱ (ሊጠልፉ፣ ተሃድሷዊ በሆነ መንገድ ሊያስኬዱ) የሚፈልጉ ኃይሎች እንዳሉ ገብቶን፤ ሊከተሉን በማይችሉት ፍጥነት ብንጓዝ አቅም እያነሳቸው እየተንጠባጠቡ ይሄዳሉ በሚል ይህን ሐሳብ የወል አድርገን ለውጡ አሸንፎ እንዲወጣ ያስቻሉ ንድፎች የተቀመሩበት ቅጽ ነው። የመደመር ትውልድ የተሰኘው ሦስተኛው ቅጽ ከፍ እያለ መጥቶ የመደመር ሐሳብ የትውልድ ሐሳብ እንዲሆን፣ ለኢትዮጵያዊ ትውልድ የምንመኘውን እና ለኢትዮጵያ ይበጃል ያልነው ሐሳብ የተመላከተበት ነው። ቅጽ ሦስት የዘመናዊቷ ኢትዮጵያ የሚባለውን ያለፉት 100 ዓመታት ታሪክ በአምስት ምድብ በመክፈል የበየነ መሆኑን እና ለዚህም የተጠኑ ባሕርያት መኖራቸውን ያነሳል። በዚህም መሠረት የመጀመሪያው ትውልድ ወግ አጥባቂ፣ ሁለተኛው ትውልድ ህልመኛ፣ ሦስተኛው ትውልድ ውል አልባ፣ አራተኛው ትውልድ ባይተዋር፣ አምስተኛው እና አሁን ያለው ትውልድ ደግሞ የመደመር ትውልድ ተብለው ተበይነዋል። ትውልዱ በመደመር እሳቤ እንዴት እንደሚታነጽ በቅጽ ሦስት ተቀምጧል። በተጨማሪም ስለ ጥበብ፣ ውበት፣ ‘ኢሞሽናል ኢንተለጀንስ’፣ ተፈጥሮን በመገንዘብ ተስማምቶ ስለመኖር በዚሁ ቅጽ ተብራርቷል። ብዙ ጊዜ መንግሥታት ያልደፈሩትና የመደመር ትውልድ ደፍሮ ካነሳቸው ሐሳቦች አንዱ የመካከለኛው ምሥራቅ እና ቀይ ባሕር ጉዳይ ነው። የቀይ ባሕር ጉዳይ ሰሞኑን የተነሳ የሚመስላቸው ሰዎች አሉ። በአጠቃላይ የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት ከትውልዱ ምን ይጠበቃል?፣ ምን የቤት ሥራ አለበት?፣ ምን ቢከውን ነው የበለጸገች፣ የተሻለች ፣ የላቀች ኢትዮጵያን መፍጠር የሚችለው የሚለውን ሐሳብ የመደመር ትውልድ በዝርዝር ዳስሷል። አሁን የተሰናዳው አራተኛው ቅጽ የመደመር መንግሥት ይባላል። በዘመናዊት ኢትዮጵያ ያሉ መንግሥታት የመንግሥታቸውን ቅርጽ፣ የመንግሥታቸውን እሳቤ፣ የመንግሥታቸውን አደራረግ በዚህ መንገድ ሠንደው አስቀምጠው አያውቁም። የመደመር መንግሥት አቀራረብ እና ዝግጅት በኢትዮጵያ ታይቶ አያውቅም። በአፍሪካ ደረጃም በእንደዚህ ዓይነት መልክ መንግሥታቸው ያለው እሳቤ፣ ያተገባበር ስልቱን፣ የሚከወንበትን መንገድ፣ ሊያሳካ የሚያስበውን ግብና ውጤት በዝርዝር ያስቀመጠ እና ለሕዝቡም የገለጸ መንግሥት የለም። ይህ በራሱ ፈር ቀዳጅ ያደርገዋል። የመደመር መንግሥት ዋና ሐሳቡ በጽንስ (በንድፍ) ያየነውን መደመር፣ በፍልስፍና ያየነውን መደመር፣ ታሪኩንና ጉዞውን ያየነውን መደመር፣ ትውልድን እንዴት እንደሚሠራ ያየነውን መደመር ተቋማዊ ቅርጽ እንዲይዝ ያደርገዋል። መንግሥታዊ ቅርጽ እንዲይዝ የሚያደርገው ይህ ሠነድ ነው፤ ሐሳቡ ከግል፣ ከቡድን ወጥቶ እንደ መንግሥት እሳቤው እንዴት እንደሚተገበር በዝርዝር ያስቀምጣል። አንደኛ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ የሚታየው ከዓለም ጋር የት ተላለፍን? እኛ እና የተቀረው ዓለም የተላለፍነው የት ነው? ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊ ስብራቶቻችን የት ጀመሩ? በሚል እኛን ከዓለም የለዩንን ነገሮች በዝርዝር ያነሳል። ኋላ ለመቅረታችን ምክንያት የሆኑ ፈተናዎች፣ ተግዳሮቶች ምንድን ናቸው? የሚሉትን በዝርዝር ያትታል። በተጨማሪም በእኛ እና በዓለም መካከል የተፈጠረውን ክፍተት እንዴት ልናጠብበው እንችላለን? ምን ዓይነት መደመራዊ አካሄዶች ብንከተል ሊጠብብ እንደሚችል ይተነትናል። ታሪኩን ካነሳ እና ክፍተቱን ከለየ በኋላ አይተውም፤ መጥበብ የሚችሉበትን መንገዶችም ያመላክታል። ያን ለማድረግ ከተለመደው የመቅዳት አካሄድ ተላቅቀን መደመራዊ ፈጠራ፣ መደመራዊ ፍጥነት እና መደመራዊ የዝላይ መንገዶችን መከተል አለብን። ካልፈጠርን፣ ካልፈጠንን፣ በአንዳንድ ጉዳዮች ደግሞ ካልዘለልን በስተቀር ያንን ክፍተት ለማጥበብ እንቸገራለን ብሎ በዝርዝር ያትታል። ሐሳቡን ሲዘረዝር ከቀደሙ መንግሥታት ኃልዮቶች ጋር ራሱን ያወዳድራል። ለምሳሌ ገበያ መር ባልንበት ጊዜ የነበረውን ሁኔታ ያወዳድራል። ወይም የዕዝ ኢኮኖሚ ባልንባቸው ወቅቶች የነበረውን አሠራርና አደራረግ ያወዳድራል። ልማታዊ መንግሥት ያልንባቸውን ጊዜያትም እንዲሁ። እነዚህን ኃልዮቶች በማንሳት በንጽጽር ያነሳል። በሁለተኛነት መደመርን ፍልስፍናው አድርጎ የሚመራ መንግሥት ምን ዓይነት ባሕርያት እንዳሉት በዝርዝር ያስቀምጣል። ስለሚከተለው ስትራቴጂ እንዲሁ በዝርዝር ያትታል። ስለሚያስመዘግበው ውጤት፣ ስለሚኖረው ግንኙነት፣ የዘመነ ገጠር፣ የተሳለጠ ከተማ እንዴት መፍጠር እንደሚቻል ያነሳል። ለስኬታችን ወሳኝ ጉዳዮችንም በሦስተኛነት ያነሳል። የፖለቲካ ስክነት ለኢኮኖሚ ስምረት የሉትን ጭምር። በሌላ በኩል ዕቅዶች እንዳይሳኩ የሚያደርጉ ተግዳሮቶችንም (ችግሮችን) ያነሳል። ድልብ ሐብቶችን እየመነዘርን የምንጠቀምበትን ሁኔታና የመፍትሔ ሐሳቦችን ያመላክታል። የጋራ ትርክት መገንባት፣ ሐሳብ ላይ የሚጫወት የፖለቲካ ምኅዳርን ማስፋት ላይም ያብራራል የሚሉትን እና ሌሎች ዋና ዋና ነጥቦችንም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቃለ ምልልሳቸው ወቅት አንስተዋል።
የመደመር መንግሥት መጽሐፍ የወል እንዲሆን በርካታ ሥራዎች ተሠርተዋል - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Aug 20, 2025 345
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2017(ኢዜአ)፡-የመደመር መንግሥት መጽሐፍ ሐሳብ የወልና ገዥ እንዲሆን የሚያስቸሉትን በርካታ ሂደቶችን ያለፈ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከመጽሐፉ ጋር በተያያዘ ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ የመደመር መንግሥት መጽሐፍ ሐሳብ ጽንሰት ቀደም ያለ መሆኑን አውስተዋል። የመደመር መንግስት ጽንሰ ሐሳብ በተለያየ ደረጃ ሊተገበር እንደሚችል ያስረዱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)፤ በግል ልምምዴ መደመር ረዘም ላለ ጊዜ ከእኔ ጋር የነበረ የተለማመድኩት፣ በሠራሁባቸው መሥሪያ ቤቶች የተጠቀምኩበትና ፍሬ ያፈራሁበት ሐሳብ ነው ብለዋል። ነገር ግን ወደ መንግሥት ሐሳብ ያደገው በሂደት ነው፤ የመንግሥት አቋም ሐሳብ ለመሆንም በርከት ያለ ጊዜ ወስዶበታል ሲሉ ገልጸዋል። ወደ መንግሥት ሐሳብነት ከመሸጋገሩ በፊትም በስልጠናዎች፣ በሐሳብ መለዋወጦች፣ ሠነዶች በማገላበጥ፣ ተጨማሪ ንባቦችና ምልከታዎች መደረጋቸውን አንስተዋል። በእነዚህ ሂደቶች ውስጥም ቀመሩ እያደገ፣ እየዳበረና እየሰፋ ከመጣ በኋላ መጽሐፍ መሆን ሲጀምርና ከጀመረ በኋላም ሐሳቡን የወል ለማድረግ በርካታ ሥራዎች ተሠርተዋል ነው ያሉት። ለአብነትም ስልጠናዎች ተሰጥተዋል፣ ውይይቶች ተካሂደዋል፣ መጽሐፉ ላይ ትችቶች ተደርገዋል፤ በዚህ ሂደትም መጽሐፉ እየዳበረ እየበሰለ፣ ሙሉ ሐሳብ መያዝ እና ሊያሠራ የሚችል ንድፍ መሆን ችሏል ብለዋል። መጽሐፉ በውስጡ ወደ ኋላ መለስ ብሎ ለራሱ ህልም ትንታኔ የሚፈይዱትን ታሪኮች በመጠኑ እንደሚዳስስና ወደፊት በመራመድም የዓለምን ነገ ብሎም የእኛን በነገ ውስጥ ያለንን ጉዞ ይተነትናል ነው ያሉት። በተጨማሪም መጽሐፉን የተለየ ያደረገው ከተጨባጭ ልምድ የተቀዳ መሆኑንም ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቆይታቸው ያብራሩት። #Ethiopia #Ethiopian_News_Agecy #ኢዜአ
ጥምረቱ አቅምን በማሰባሰብ እና አንድነትን በመፍጠር የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታን ይበልጥ ማጎልበት ዋነኛ ዓላማው ነው
Aug 20, 2025 349
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 14/2017(ኢዜአ)፦ የፖለቲካ ጥምረቱ አቅምን በማሰባሰብ እና አንድነትን በመፍጠር የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታን ማጎልበት ዋነኛ ዓላማው መሆኑን የአስራ አንድ ክልላዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥምረት አስተባባሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዳሮት ጉምአ ገለጹ፡፡ አስራ አንድ ክልላዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥምረት መመስረታቸውን የገለጹ ሲሆን ጥምረት የመሠረቱ የፖለቲካ ፓርቲዎችም በዛሬው ዕለት የምስረታ ጉባኤያቸውን በማካሄድ ላይ ይገኛሉ። የጥምረቱ አስተባባሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዳሮት ጉምአ ፤ ጥምረቱ አንድነት ኃይል መሆኑን በሚያምኑ አካላት የተገነባ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ የጥምረቱ አባል ፓርቲዎች ለሀገር ሰላም፣ ዕድገትና ክብር በጋራ የሚቆሙ እና ኃላቀር የፖለቲካ ባህልን ለመቀየር እንደሚሰሩም ተናግረዋል፡፡ ፓርቲዎቹ የየራሳቸውን ዓላማ በመያዝ ለጋራ ስኬት ጥምረት መፍጠራቸውን ጠቁመው፤ የተሻለ የፖለቲካ ባህልን ለመገንባት ትልቅ ሚና የሚጫወት መሆኑንም ተናግረዋል። የፖለቲካ ፓርቲዎቹ መጣመር የተሻለች ኢትዮጵያን ለትውልድ ለማስተላለፍ እንደሚጠቅም ጠቁመው፤ ለፖለቲካ ባህል መዘመንም የበኩሉን እንደሚወጣም ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ሃይሉ በዚሁ ወቅት፤ አቅምን በማሰባሰብ ለጋራ እና ለተሻለ ዓላማ መሥራት መልካም መሆኑን ተናግረዋል። ልዩነቶችን በማክበር በጋራ መንቀሳቀስ ለጤናማ የፖለቲካ ስርዓት መዳበር ትልቅ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑንም ገልጸዋል። ጥምረቱ መጪው ሀገራዊ ምርጫ ፍጹም ተዓማኒ እንዲሆን የበኩሉን እንዲወጣ ጠይቀው፤ ቦርዱ ጥምረቱን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ሰለሞን አየለ በበኩላቸው፤ የፓርቲዎቹ ጥምረት ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ መጎልበት ትልቅ ሚና ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታም ትልቅ ሚና ያለው መሆኑን ጠቁመው፤ ጥምረቱ ዘላቂ ሰላምን ለመፍጠር እና ለሀገራዊ መግባባት ስኬታማነት የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባም ተናግረዋል። የዎቻ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ብርሃኑ ዘለቀ በሰጡት አስተያየት ጥምረቱ ለተሻለ የፖለቲካ ስርዓት ግንባታ ትልቅ ፋይዳ ያለው ነው ብለዋል፡፡ ተበታትኖ የሚገኘውን የሰው ኃይል፣ ቁሳቁስ፣ እውቀትና ቴክኖሎጂ በማሰባሰብ ለሀገር ዕድገት የበኩላቸውን ለመወጣት እንደሚያግዛቸው ተናግረዋል፡ የከፋ አረንጓዴ ፓርቲ ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ወንድሙ ወዱዌሮ በበኩላቸው ጥምረቱ ለመድበለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታና ለሀገር ዕድገት ትልቅ ጥቅም ያለው መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ጥምር ፓርቲ የመሰረቱት አገው ለፍትሕና ዴሞክራሲ፣አገው ብሔራዊ ሸንጎ፣ ትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ የዶንጋ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ ሞቻ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ አርጎባ ብሔረሰብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ፣ አፋር ነፃ አውጭ ግንባር ፓርቲ፣ ከጋሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣የካፋ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት፣ ካፋ አረንጓዴ ፓርቲ እና የጋምቤላ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ናቸው፡፡
አስራ አንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥምረት መሠረቱ
Aug 20, 2025 387
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 14/2017(ኢዜአ)፦ አስራ አንድ ክልላዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጥምረት መመስረታቸውን አስታወቁ። ጥምረት የመሠረቱ የፖለቲካ ፓርቲዎችም በዛሬው ዕለት የምስረታ ጉባኤያቸውን በማካሄድ ላይ ይገኛሉ። በዚህም የፖለቲካ ፓርቲዎቹ ልዩነቶቻቸውን በማክበር ለጋራ ዓላማ ተጣምረው እንደሚሰሩም ተጠቁሟል። የጥምረቱ አስተባባሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዳሮት ጉምአ እንዳሉትም፤ የፖለቲካ ፓርቲዎቹ በጋራ መሰባሰብ አንድነት ሃይል መሆኑን በተግባር ያሳያል ብለዋል። ፓርቲዎቹ የየራሳቸውን ዓላማ በመያዝ ለጋራ ስኬት ጥምረት መፍጠራቸው ጠቁመው፤ የተሻለ የፖለቲካ ባህልን ለመገንባት ትልቅ ሚና የሚጫወት መሆኑንም ተናግረዋል። የፖለቲካ ፖርቲዎቹ መጣመር የተሻለች ኢትዮጵያን ለትውልድ ለማስተላለፍ እንደሚጠቅም ጠቁመው፤ ለፖለቲካ ባህል መዘመንም የበኩሉን እንደሚወጣም ተናግረዋል። የመተሣሠብ እና የመተባበር ዕድል የሚፈጠር እንዲሁም የሐሳብ ፖለቲካን ማንገስ ሌላኛው የጥምረቱ ዓላማ መሆኑንም ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ ሃይሉ በዚሁ ወቅት፤ አቅምን በማሰባሰብ ለጋራ እና ለተሻለ ዓላማ መሥራት መልካም መሆኑን ተናግረዋል። ልዩነቶችን በማክበር በጋራ መንቀሳቀስ ለጤናማ የፖለቲካ ስርዓት መዳበር ትልቅ አስተዋጽኦ ያለው መሆኑንም ገልጸዋል። ጥምረቱ መጪው ሀገራዊ ምርጫ ፍጹም ተዓማኒ እንዲሆን የበኩላቸውን እንዲወጡ ጠይቀው፤ ቦርዱ ጥምረቱን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኑን አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፖርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ሰለሞን አየለ በበኩላቸው፤ የፓርቲዎቹ ጥምረት ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ መጎልበት ትልቅ ሚና ያለው መሆኑን ገልጸዋል። ለመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታም ትልቅ ሚና ያለው መሆኑን ጠቁመው፤ ጥምረቱ ዘላቂ ሰላምን ለመፍጠር እና ለሀገራዊ መግባባት ስኬታማነት የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባም ጠቁመዋል። ጥምር ፓርቲ የመሰረቱት አገው ለፍትሕና ዴሞክራሲ፣አገው ብሔራዊ ሸንጎ፣ ትግራይ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ የዶንጋ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ ሞቻ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ አርጎባ ብሔረሰብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ፣ አፋር ነፃ አውጭ ግንባር ፓርቲ፣ ከጋሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣የካፋ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት፣ ካፋ አረንጓዴ ፓርቲ እና የጋምቤላ ህዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ ናቸው፡፡
ችግሮችን በምክክር ለመፍታት በሚደረገው ጥረት ምሁራን ተሳትፏቸውን ማጠናከር ይጠበቅባቸውል- ኮሚሽነር ዮናስ አዳዬ (ዶ/ር)
Aug 20, 2025 225
ባሕርዳር፤ ነሐሴ 14/2017(ኢዜአ)፡- ችግሮችን በምክክር በመፍታት ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን በሚደረገው ጥረት ምሁራን ተሳትፏቸውን ይበልጥ አጠናክረው ሚናቸውን መወጣት እንደሚጠበቅባቸው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር ዮናስ አዳዬ(ዶ/ር) ገለጹ። ኮሚሽኑ በአማራ ክልል ከሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች ምሁራን ጋር በምክክሩ አስፈላጊነት፣ እስካሁን በተገኙ ስኬቶችና በቀጣይ ስራዎች ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ በባሕር ዳር ከተማ እያካሄደ ነው። በመድረኩ ላይ ኮሚሽነር ዮናስ አዳዬ(ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ ዘላቂ ሰላም የሰፈነባት ሀገር ለመገንባት ምክክርን ባህል በማድረግ ችግሮችን በጋራ መፍታት ያስፈልጋል። ለዚህም በሃገራዊ ምክክር የሚስተዋሉ ችግሮችን በመፍታት ህዝቡ በአብሮነት፣ በፍቅርና በመተሳሰብ እንዲኖር የሚያስችል ምዕራፍ መከፈቱን ገልጸዋል። ችግሮችን በምክክር መፍታት በሚደረገው ጥረት ምሁራን በእውቀት የታገዙ ምርምሮችን በማካሄድና የሌሎች ሀገራትን ተሞክሮ በማምጣት ተሳትፏቸውን ይበልጥ አጠናከረው ሚናቸውን መወጣት እንደሚጠበቅባቸው። ምሁራን በሀገራችን ዘላቂ ሰላምን በማስፈን ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት የምትችሉትን ሁሉ ማበርከት አለባችሁ ብለዋል። አባቶቻችን በየዘመናቱ ባካሄዱት ተጋድሎ ዳር ድንበሯ የተከበረ ሀገር አስረክበውናል ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ሰላሟ የሰፈነና ያደገች ሀገር እንድትኖረን ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ሲሉም መልዕክት አስተላልፈዋል። ምሁራን በምክክሩ ያልተሳተፉ ወገኖችን በማግኘት የምክክር ኮሚሽኑን ዓላማ በማስረዳት የመፍትሄው አካል እንዲሆኑ የማስቻል ስራ ማከናወን እንዳለባቸውም አንስተዋል። የውይይት መድረኩ ከዛሬ ጀምሮ ለሁለት ቀናት እንደሚቆይ ተመልክቷል።
የአካባቢያችንን ሰላም በዘላቂነት በማስጠበቅ ልማትን ለማፋጠን ተሳትፏችንን እናጠናክራለን -በኢሉአባበር ዞን ነዋሪዎች
Aug 19, 2025 242
መቱ፤ ነሐሴ 13/2017 (ኢዜአ)፡- የአካባቢያቸውን ሰላም በዘላቂነት አስጠብቆ በማስቀጠል ልማትን ለማፋጠን ተሳትፏቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በኢሉአባበር ዞን ነዋሪዎች ገለጹ። ከዞኑ ሁሉም ወረዳዎች የተውጣጡ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ያሳተፈ የሰላምና ልማት ኮንፈረንስ በመቱ ከተማ ተካሂዷል። የኮንፈረንሱ ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት፤ በዞኑ ሰላምን አፅንቶ ለማስቀጠል የፀጥታ አስከባሪ አካላትን በመደገፍ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። የተጀመሩ አዳዲስ የልማት ተግባራት ተጠናክረው እንዲቀጥሉም እያገዙ መሆኑን አመልክተዋል። ከተሳታፊዎቹ ወስጥ አቶ በንቲ ጂማ፣ ለየትኛው ልማት ስራ ሰላም ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ በየአካበቢያቸው ከጸጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት ሰላማቸውን እየጠበቁ መሆኑን አስታውቀዋል። ሌላው አቶ ደጀኔ ከበደም በበኩላቸው፤ ሰላምን ማስከበር በጸጥታ አካላት ብቻ ባለመሆኑ ተደራጅተው ሰላማቸውን ለማፅናት በትብብር እየሰሩ መሆኑን ገልጸዋል። የአካባቢያቸውን ሰላም በዘላቂነት አፅንቶ በማስቀጠል ልማትን ለማፋጠን ሲያዳርጉ የቆዩትን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩ የኮንፈረንሱ ተሳታፊዎች ተናግረዋል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳልካቸው ተፈሪ ፤ በዞኑ በተለይ በግብርናው ዘርፍ እየተተገበሩ በሚገኙ ኢኒሼቲቮች አበረታች ውጤቶች እያስመዘገቡ ነው ብለዋል። በሁሉም ዘርፎች የተጀመሩትን ልማቶች በማጠናከር ወደተሻለ ምዕራፍ ለመሸጋገርም ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል። የተጀመረውን የልማት ስራ የበለጠ ለማፋጠን ሰላም ዋነኛና ወሳኝ ጉዳይ በመሆኑ የዞኑ ነዋሪዎች ከጸጥታ አካላት ጋር በመሆን ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የማርቺንግ ባንድ ፌስቲቫል ለመጀመሪያ ጊዜ ትሳተፋለች-መከላከያ ሚኒስቴር
Aug 18, 2025 355
አዲስ አበባ፤ ነሐሴ 12/2017 (ኢዜአ)፡-ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የማርቺንግ ባንድ ፌስቲቫል ለመጀመሪያ ጊዜ እንደምትሳተፍ የመከላከያ ሰራዊት ስነ-ልቦና ግንባታ ዋና ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል እንዳልካቸው ወልደሚካኤል ገለጹ። በመከላከያ ሚኒስቴር የመከላከያ ሰራዊት ስነ-ልቦና ግንባታ ዋና ዳይሬክተር ሜጄር ጄኔራል እንዳልካቸው ወልደሚካኤል ፌስቲቫሉን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት በሁሉም ዘርፎች ያለውን ተቀባይነትና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነት ለመጨመር ለሚያስችሉ ስራዎች ትኩረት መሰጠቱን ገልጸዋል። በተጨማሪም የሰራዊቱን አቅምና ልዩ ችሎታ የሚያጎለብቱ አሰራሮችን ተግባራዊ ማድረግ አንዱና ዋነኛው ስለመሆኑም አብራርተዋል። ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያገኘችውን ተቀባይነት ተከትሎ በዓለም አቀፍ የማርቺንግ ባንድ ፌስቲቫል ተሳታፊ እንድትሆን ከአንድ ዓመት በፊት ጥሪ መቅረቡን አስታውሰዋል። በዚህም የመከላከያ ኪነ-ጥበባት ዳይሬክቶሬት የማርቺንግ ቡድን በሩሲያ ሞስኮ በሚካሔደው ዓለም አቀፍ ፌስቲቫል ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ እንደሚሳተፍ አስታውቀዋል። ሃምሳ አባላት የያዘው ማርቺንግ ቡድኑ ዛሬ ምሽት ወደ ሩሲያ ለሚያደርገው ጉዞ አስፈላጊውን ዝግጅት ማጠናቀቁን አብራርተዋል። ቡድኑ ለሁለት ሳምንታት በሚኖረው ቆይታ የኢትዮጵያን የመከላከያ ሰራዊት ማርቺንግ ብቃትና አቅም ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ የሚያስተዋውቅ ስለመሆኑም አንስተዋል። ፌስቲቫሉ ከማርቺንግ ትርዒት በዘለለ ለአገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መጨመር፣ ለባህልና ልምድ ልውውጥ ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለው አብራርተዋል።