ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
በበጀት አመቱ በከተማዋ በተከናወኑ ስኬታማ የሰላም ተግባራት የህብረተሰቡ ተሳትፎ ከፍተኛ ነበር - የከተማዋ የምክር ቤት አባላት
Jul 11, 2025 44
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ በበጀት አመቱ በከተማዋ በተከናወኑ ስኬታማ የሰላም ተግባራት የህብረተሰቡ ተሳትፎ ከፍተኛ እንደነበር የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አባላት ተናገሩ። 3ኛው የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ እና የበጀት አመቱ ማጠቃለያ ስብሰባ እየተካሄደ ነው። በስብሰባው ከንቲባ አዳነች አቤቤ የ2017 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት እና የ2018 በጀት ዓመት ዋና ዋና አቅጣጫዎችን ለምክር ቤቱ አቅርበዋል። በዚሁ ጊዜ በ2017 በጀት ዓመት የከተማዋን ሰላም በማስጠበቅ፣ የነዋሪዎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ከማሳደግ እንዲሁም አህጉራዊና ዓለም-አቀፋዊ ሁነቶችን በማስተናገድ ስኬታማ ሥራዎች መሰራታቸውን ነው ያብራሩት። በከተማዋ ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ በርካታ የጸጥታና የወንጀል ድርጊቶችን በመለየትና አስቀድሞ በመከላከል ብሎም ህጋዊ እርምጃዎችን መውሰድ መቻሉን አንስተዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት አባላትም የከተማዋን ሰላምና ደህንነት ከማረጋገጥ አንጻር የተከናወኑት ተግባራት ስኬታማ መሆናቸውን ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊና የምክር ቤቱ አባል ሊዲያ ግርማ በበጀት ዓመቱ በከተማዋ ሰላም በመረጋገጡ የልማት ስራዎች ስኬታማ በሆነ መልኩ እንዲከናወኑ በትኩረት መሰራቱን ገልጸዋል። የከተማው ነዋሪ ህብረተሰብም በወንጀል መከላከል ሂደትና ሰላም በማስጠበቅ ሂደት ላይ የነበረው ተሳትፎ በየጊዜው እየጎለበተ መምጣቱን እንዲሁ። ሰላም ለአንድ ሀገር ሁለንተናዊ ልማት የማይተካ ሚና አለው ያሉት ደግሞ ሌላዋ የምክር ቤት አባል ወርቅነሽ ምትኩ (ዶ/ር) ናቸው። በከተማዋ ለተመዘገቡ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ለውጦች የሰላምና ጸጥታ መረጋገጥ ትልቅ ሚና መጫወቱንም ጨምረው ተናግረዋል፡፡ ሌላው የምክር ቤት አባል ኢቲሳ ደሜ(ዶ/ር) ህዝብን ያሳተፈ የሰላምና ልማት ሥራ የተሻለ ውጤት እንደሚያመጣ አዲስ አበባ ማሳያ ናት ብለዋል። ከተማዋ የአህጉራዊና አለም አቀፋዊ ተቋማት መቀመጫና የአፍሪካ መዲና በመሆኗ ዘላቂ ሰላምን በማረጋገጥ በኩል ህብረተሰቡ ቀጣይነት ያለው ድጋፉንና ተሳትፎውን ማስቀጠል እንደሚገባ በመጥቀስ። በከተማዋ ሰላምና ልማትን ለማረጋገጥ የተጀመሩ ሥራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉና የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት እንዲረጋገጡ የምክር ቤቱ አባላት ድጋፍና ክትትላቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጸዋል። የከተማዋን ሰላም በማስቀጠል ሂደትም ነዋሪው ተሳትፎውን አጠናክሮ እንዲቀጥል የምክር ቤት አባላቱ ጥሪ አቅርበዋል።
በህብረብሔራዊ አንድነት ላይ ያተኮረ ትርክት ግንባታ በውጤታማነት ተጠናክሮ ቀጥሏል - ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር)
Jul 11, 2025 71
አርባምንጭ ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡-በሀገሪቱ በህብረብሔራዊ አንድነት ላይ ያተኮረ ትርክት ግንባታ በውጤታማነት ተጠናክሮ መቀጠሉን የብልጽግና ፓርቲ የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ ሃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) ተናገሩ ። የብልጽግና ፓርቲ ዋና ጽህፈት ቤት የህዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዘርፍ የ2017 በጀት ዓመት አፈጻጸምና የ2018 ዕቅድ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተገመገመ ነው። የብልጽግና ፓርቲ ዓለም አቀፍና የሕዝብ ግንኙነት ዘርፍ ኃላፊ ቢቂላ ሁሪሳ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት ኢትዮጵያ በኢኮኖሚው በፖለቲካውና፣ በዲፕሎማሲው ዘርፍ በዓለም አደባባይ ፈጣን ለውጥ እያስመዘገበች ትገኛለች ብለዋል። ይህን ለማሳካትም የተረጋጋ የፖለቲካ ምህዳር በመፍጠር በህዝቦች መካከል ወንድማማችነትና እህትማማችነት እየተጠናከረ የመጣበት ዓመት ነው ሲሉም ገልጸዋል። የሀገርን እድገት ወደ ኋላ ለመመለስ የሚጥሩ አካላት በህዝብና በመንግስት ትብብር ሴራቸው እየከሸፈ መምጣቱንም ገልጸዋል። በህብረብሔራዊ አንድነት ላይ ያተኮረ ትርክት ግንባታ ሂደትም ውጤታማ በሆነ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን ያነሱት ቢቂላ (ዶ/ር) ''እስካሁን የተመዘገበውን ስኬት ለማስቀጠል አበክረን እንሠራለን'' ብለዋል። በብልጽግና ፓርቲ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ገብረመስቀል ጫላ በበኩላቸው ፓርቲው የህዝቡን ሁለንተናዊ ብልጽግና እያረጋገጠ ይገኛል ብለዋል። የብሔር ብሔረሰቦችን መብት በማስከበር የተረጋጋች ሀገር የመገንባት ሂደቱም በተሻለ መልኩ እየተከናወነ መሆኑን አብራርተዋል። በቀጣይም የተጀመሩ ልማቶችን በማስቀጠል የህዝቡን ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ ትኩረት ተሰጥቶ እንደሚሠራ ጠቁመዋል። ለሁለት ቀናት በተዘጋጀው መድረክ ከሁሉም ክልሎች የፓርቲው ህዝብ ግንኙነት ኃላፊዎችና ባለሙያዎች እየተሳተፉ ይገኛሉ።
በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤታማ ስራዎች ወደ ላቀ ደረጃ የማሸጋገሩ ተግባር ይጠናከራል
Jul 10, 2025 100
ሐረር፤ሐምሌ 3/2017 (ኢዜአ)፡-በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተመዘገቡ ውጤታማ ስራዎች ወደ ላቀ ደረጃ የማሸጋገሩ ተግባር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል በብልፅግና ፓርቲ የዋና ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለስ ዓለሙ ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ በሐረር ከተማ ለሁለት ቀናት ሲያካሂደው የቆየው የ2017 እቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2018 እቅድ ተግባቦት መድረክ ዛሬ ተጠናቋል። በመድረኩ የፌደራልና የክልል የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ አመራሮች እንዲሁም የፓርቲው የወጣቶችና ሴቶች ክንፍ ተሳትፈዋል። በብልፅግና ፓርቲ የዋና ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለስ ዓለሙ በወቅቱ እንደተናገሩት፥ በ2017 በጀት ዓመት የዴሞክራሲ ባህል እሴትን ለማጠናከር የሚያስችሉ ውጤታማ ተግባራት ተከናውነዋል። የፖለቲካ ፓርቲዎች በትብብር ከመስራት አንጻር በሁሉም ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች በጋራ ምክር ቤቶች በመደራጀት አብሮ የመስራት ባህል እየዳበረ መምጣቱን ጠቅሰዋል። ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የተጀመሩ ስራዎች አዲስ ባህልና ልምድ እያመጡ ስለመሆኑም አንስተዋል። የጋራ ስራዎቹ ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸው፤ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ለዴሞክራሲ ባህል ግንባታ በቁርጠኝነት መስራታቸውን አጎልብተው እንዲቀጥሉም አመልክተዋል። በአሁኑ ወቅት በየደረጃው ያለው የመንግስት አካላትና ሲቪል ማህበረሰብ በጋራና በቅንጅት የሚሰሩበት ጅምር ሁኔታ መፈጠሩን ጠቅሰዋል። በተለይ የወጣቶችና ሴቶች አስተዋጽኦን ለማላቅና ተሳትፏቸውን ይበልጥ ለማሳደግ ብሎም ተጠቃሚነታቸውን ለማጎልበት መድረኩ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም አንስተዋል። በቀጣይም ትኩረት በሚሹ ጉዳዮች ላይ በተቀመጡ አቅጣጫዎች መሰረት ትኩረት ተሰጥቶ እና ባህል አድርጎ እንደሚሰራም አመላክተዋል።
የከተማው ነዋሪዎች ሰላምን ለማፅናት እያበረከቱት ያለው አስተዋጽኦ ለኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት እንቅስቃሴው ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Jul 10, 2025 98
ደብረብርሃን ፤ ሐምሌ 3/ 2017 (ኢዜአ)፡- የደብረ ብርሃን ከተማ ነዋሪዎች ከጸጥታ ሃይሉ ጎን በመሰለፍ በአካባቢው ሰላምን ለማፅናት እያበረከቱት ያለው አስተዋጽኦ ለኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት እንቅስቃሴው ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የከተማ አስተዳደሩ አስታወቀ። የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር በአካባቢው ሰላምን ለማፅናት አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት የእውቅና እና የምስጋና መርሃ ግብር አካሂዷል። በመርሃ ግብሩ ላይ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት እንደገለጹት፤ የጸጥታ ሃይሉ ከሕብረተሰቡ ጋር በመተባበር ሰላም እንዲከበር ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል። በዚህም በከተማዋ የሚካሄዱ የኢንዱስትሪ፣ የኢንቨስትመንትና የንግድ ስራዎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ጠቅሰዋል። ይህም ስራ እድል እንዲስፋፋ፣ የገቢና ሌሎች የልማት ዘርፎች ውጤታማ እንዲሆኑ ምቹ መደላድል መፍጠሩን ገልጸዋል። በከተማዋ አሁን ላይ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎች እየተካሄዱ እንደሚገኙ አስረድተዋል። የልማት ሁሉ መሰረት የሆነውን ዘላቂ ሰላም ለማስፈን በሚደረገው ጥረት ሁሉ ሕብረተሰቡ ከጸጥታ ሃይሉ ጎን በመሰለፍ የተለመደ ድጋፉን አጠናክሮ እንዲቀጥልም መልዕክት አስተላልፈዋል። የእውቅና እና የምስጋና መርሃ ግብሩ ዓላማም የከተማው ነዋሪዎች ከጸጥታ ሃይሉ ጎን በመሰለፍ የህግ ማስከበር ስራው ይበልጥ በውጤታማነት በማስቀጠሉ ሂደት ድጋፋቸውን እንዲያጠናክሩ ለማበረታታ መሆኑን ተናግረዋል። ከህግ አስከባሪዎች መካከል ሀምሳ አለቃ ሰይፈ ደምሰው በሰጡት አስተያየት፤ ሰላምን አፅንቶ በማስቀጠል ለልማት የተፈጠረው ምቹ ሁኔታ ይበልጥ ለማጠናከር ከሕብረተሰቡ ጋር ተቀናጅተወ በትኩረት እንደሚሰሩ ተናግረዋል። ሌላው የመርሃ ግብሩ ተሳታፊ ፈለቀ በየነ በበኩላቸው፤ የአካባቢውን ሰላም በማፅናት የልማት ስራዎቻቸው ተጠናክረው እንዲቀጥሉ በቁርጠኝነት እንሰራለን ብለዋል። በመርሃ ግብሩ ላይ የጎዳና ላይ ትርኢቶችና ሌሎች ዝግጅቶች ተካሂደዋል።
በብሔረሰብ አስተዳደሩ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያሳድጉ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል
Jul 10, 2025 81
ሰቆጣ ፤ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተግባራት መከናወናቸውን የብሔረሰብ አስተዳደሩ አስታወቀ። የብሔረሰብ አስተዳደሩ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸምን የሚገመግምና የቀጣይ 90 ቀናት ዕቅድ ማስተዋወቂያ መድረክ በሰቆጣ ከተማ እየተካሄደ ነው። የብሔረሰብ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሃይሉ ግርማይ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት በበጀት ዓመቱ ህብረተሰቡን ያሳተፈ የሰላምና ፀጥታ ተግባር በመካሄዱ የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ ተችሏል። በልማት ሥራም ለመልካም አስተዳደር ምክንያት ሆኖ የቆየው የሰቆጣ አዳሪ ትምህርት ቤትን ጨምሮ የስርዓተ ምግብን ለማሻሻል በዓመት ከ360 ሺህ በላይ ጫጩት ማስፈልፈያ ማዕከል ግንባታ ስራን ማከናወን እንደተቻለ ገልጸዋል። በተጨማሪም የመስኖ መሰረተ ልማትን በማስፋፋት የግብርና ምርታማነት እንዲያድግ መሰራቱን ጠቁመው፣ የመኽር እርሻ ምርታማነትን ለማሳደግም በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። በፌደራል፣ በክልልና በወረዳ በጀት እየተገነቡ ያሉ መሰረተ ልማቶች በተቀመጠላቸው ጊዜ በጥራት ተገንብተው እንዲጠናቀቁ የድጋፍና ክትትሉ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። የአመራሩን የማስፈፀም አቅም ይበልጥ በማሳደግ በበጀት ዓመቱ የተገኙ ስኬቶችን በአዲሱ በጀት ዓመትም ለመድገም ከምንጊዜውም በላይ በቁርጠኝነት እንደሚሰራም አቶ ሃይሉ አስረድተዋል። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የፀጥታ ችግር ባለባቸው አካባቢዎች ጭምር ያልተቋረጠ የጤና አገልግሎት መስጠት መቻሉን የተናገሩት ደግሞ የብሔረሰብ አስተዳደሩ ጤና መምሪያ ሃላፊ አቶ አሰፋ ነጋሽ ናቸው። በበጀት ዓመቱ በስርዓተ ምግብ ማሻሻል እንዲሁም የወባ እና ሌሎች ተላላፊ በሽታዎችን በመከላከልና በማከም በተሰራው ስራም የከፋ ችግር ሳይደርስ ማለፉንም ተናግረዋል። የእናቶችና ህፃናት ህክምና ማዕከልን ጨምሮ 42 የጤና ፕሮጀክቶች እየተገነቡ መሆናቸውን የተናገሩት አቶ አሰፋ፤ በጤና ተቋማቱ ዜጎችን የጤና አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። የብሄረሰብ አስተዳደሩ የግብርና መምሪያ ሃላፊ አቶ አዲስ ወልዴ በበኩላቸው "በብሔረሰብ አስተዳደሩ በመስኖ ከለማው መሬት ከ700 ሺህ ኩንታል በላይ ምርት ተሰብስቧል ብለዋል። ይህም የአካባቢውን ገበያ ለማረጋጋት ማገዙን ተናግረዋል። በበጋው ወቅት በ369 ተፋሰሶች ላይ ህብረተሰቡን ያሳተፈ የተፈጥሮ ሃብት ልማት ሥራ መካሄዱን ጠቁመው፣ የለሙትን ተፋሰሶች በስነ እፅዋት ዘዴ ለማጠናከርም ችግኞች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። በመድረኩ ላይ የክልል፣ የብሔረሰብ አስተዳደሩና የወረዳ አመራሮች ተሳትፈዋል።
የኢትዮጵያና ዛምቢያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት በተለያዩ መስኮች ተጠናክሮ ቀጥሏል - አምባሳደር ሮዝ ሳካላ
Jul 10, 2025 102
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ እና በዛምቢያ መካከል ያለው ረጅም ጊዜ ያስቆጠረ ግንኙነት በተለያዩ መስኮች ተጠናክሮ መቀጠሉን በኢትዮጵያ የዛምቢያ አምባሳደር ሮዝ ሳካላ ገለጹ። በኢትዮጵያ የዛምቢያ አምባሳደር ሮዝ ሳካላ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ኢትዮጵያ እና ዛምቢያ ዘላቂ እና ዘርፈ-ብዙ ግንኙነት እንዳላቸው ገለጸዋል። ይህም ግንኙነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ እና በተለያዩ ዘርፎችም እያደገ መምጣቱን ተናግረዋል። በተለይም ዛምቢያ ኤምባሲዋን በኢትዮጵያ ከከፈተችበት ጊዜ አንስቶ የሁለቱ አገሮች አጋርነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጎለበተ ከመምጣቱም በላይ የተለያዩ የትብብር ስራዎችም እየተጠናከረ እንደሚገኝ ተናግረዋል። እ.አ.አ በ2017 ሁለቱ ሀገራት የጋራ ኮሚሽን ማቋቋማቸውን ገልጸው፤ ይህም ተጨባጭ ጥቅሞችን ማስገኘቱን ጠቁመዋል። ሁለቱ ሀገራት ከፍተኛ አቅም እንዳላቸው ገልጸው፤ ከሁለቱም ወገኖች የተውጣጡ የንግድ ባለሙያዎችን እና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን በማሰባሰብ ግንኙነታቸውን የበለጠ ለማሳደግ ጥረት መደረጉን አንስተዋል። የጋራ ኮሚሽኑ በንግድና ኢንቨስትመንት በተለይም በግብርናና በአየር ትራንስፖርት ዘርፍ ያለውን ትስስር እንደሚያጠናክር ጠቁመዋል። ዛምቢያ የአፍሪካን አንድነት ለማጎልበት እና አህጉራዊ አጀንዳዎችን ለማራመድ በተለያዩ መድረኮች በማደራጀት እና በመሳተፍ ንቁ ተሳትፎ እያደረገች መሆኑን ተናግረዋል ። አፍሪካ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ውስጥ ቋሚ ውክልና አለማግኘቷ ኢ-ፍትሃዊ ነው ብለዋል። ዛምቢያ ለቀጣናው ኢኮኖሚያዊ ውህደት ትልቅ አስተዋፅዖ እንዳደረገች ገልፀው፤ ፓን አፍሪካኒዝም እንደ መሰረታዊ መርህ እና ከእነዚህ ጥረቶች ጀርባ አንቀሳቃሽ ሃይል ሆኖ ያገለግላል ብለዋል። የአፍሪካ ህብረት አጀንዳ 2063 ለአፍሪካ በርካታ እድሎችን የሚሰጥ ወርቃማ አጀንዳ መሆኑን ገልጸው፤ በትብብር መተግበር እንደሚገባ አሳስበዋል።
የምርምር ባህልን ማሳደግና ፈጠራን ማበረታታት ቀጣይነት ላለው ሀገራዊ እድገት ወሳኝ ነው-አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ
Jul 10, 2025 106
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ የምርምር ባህልን ማሳደግና ፈጠራን ማበረታታት ቀጣይነት ላለው ሀገራዊ እድገት ወሳኝ መሆኑን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጹ። አምስተኛው ዓመታዊ የፓርላማ ጥናትና ምርምር ኮንፈረንስ "አካታችና ጠንካራ የፓርላማ ስርዓት ለሀገር በቀል እውቀትና ቀጣይነት ላለው ልማት" በሚል መሪ ሀሳብ መካሄድ ጀምሯል። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ በጉባኤው መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት፥ በየዓመቱ የሚካሄደው የምርምር ጉባኤ ለእውቀት መፍለቅ፣ለምርምርና ጥናት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው። ጉባኤው ምክር ቤቱ ለተሻለ ህግ ማውጣት፣ ለውጤታማ ክትትልና ቁጥጥር እንዲሁም ለተሳካ የፓርላማ ዲፕሎማሲ የሚያስፈልገውን መረጃና ትንተና እንዲያገኝ እድል መፍጠሩን አስታውሰዋል። በምጣኔ ሃብት፣ፖለቲካ፣ማህበራዊና በቴክኖሎጂ ዘርፎች የሚደረጉ ጥናትና ምርምሮች ሀገራዊ አቅምን ለመገንባትና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ ወሳኝ ናቸው ብለዋል። ምርምር ለማንኛውም አገራዊ ልማትና እድገት መሰረት በመሆኑ በተቋምና በሀገር ደረጃ የላቀ እድገት ለማስመዝገብ ለጥናትና ምርምር ትኩረት መስጠት ተገቢ መሆኑን አስገንዝበዋል። የምርምር ባህልን ማሳደግ፣ፈጠራን ማበረታታትና እውቀትን በተግባር ማዋል ቀጣይነት ላለው እድገት ወሳኝ መሆኑን በመጠቆም በተለይም ለህግ አውጪ አካል ስራዎች የምርምር ሚና የላቀ እንደሆነም ጠቁመዋል። ምክር ቤቱ የሚወስናቸው ውሳኔዎች፣የሚያወጣቸው ህጎችና የሚያደርገው የክትትልና ቁጥጥር ስራ ጥናትና ምርምር ላይ የተመሰረቱ እንዲሆኑ ሚናውን አጠናክሮ ይቀጥላል ያሉት። እንደ አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጻ፥ የሚወጡ ህጎችን ተቀባይነት እንዲኖራቸው በጥናት ላይ የተመሰረተ የህዝብ ፍላጎት፣አስተያየትና ቅሬታን በመሰብሰብና በመተንተን በህግ አወጣጥ ሂደት ውስጥ ማካተት ያስፈልጋል። በተመሳሳይ ምክር ቤቱ መንግስት የሚሰራቸውን ስራዎች ለመከታተል፣ የበጀት አጠቃቀም ለመቆጣጠርና የመንግስት ፖሊሲዎችን ውጤታማነትን ለመገምገም ጥልቅ ትንተና ማድረግ ተገቢ ነው ብለዋል። ምክር ቤቱ ለምርምር ትኩረት በመስጠት፣የምርምር ጉባኤዎችን በማዘጋጀትና የፓርላማ የምርምር ትስስር በማቋቋም ከምርምር ተቋማት ጋር ያለውን ግንኙነት ማጠናከሩንም ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሳሙኤል ክፍሌ(ዶ/ር) በበኩላችው፥ የቴክኖሎጂ ዕድገትን ተከትሎ የተፈጠረው የድህረ እውነት ዓለም አሉታዊ ተጽእኖ እያሳደረ እንደሚገኝ አንስተዋል። ይህን ለመቀልበስ በጥናት ምርምር ላይ የተመሰረተ ሥራ እና ጠንካራ ፓርላማ መገንባት እንደሚያስፈልግ አመላክተዋል። በምርምር ጉባኤው ጥናታዊ ፅሁፍ ያቀረቡት በጅማ ዩኒቨርሲቲ የማህበራዊ ሳይንስ ተመራማሪ እውነቱ ሃይሉ (ዶ/ር)፥ ኢትዮጵያ ለዘመናት ፀንታ የቆየችው በራሷ ዕውቀትና እውነት ውስጥ በመኖሯ ነው ብለዋል። ምክር ቤቱ በሚያወጣቸው የህግ ማዕቀፎች ውስጥ ሀገር በቀል እውቀቶችን ማካተት አለበት ያሉት ተመራማሪው፥ የሀገር በቀል እወቀቶችን ፋይዳ ማስገንዘብም እንደሚገባ አስረድተዋል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የህዝብ አስተዳደርና ኢኮኖሚ መምህርና ተመራማሪ ዳንኤል በየራ በበኩላቸው፥ ከሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አካታችነት አንጻር የተገኙ ውጤቶችና ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ጥናታዊ ፅሁፍ አቅርበዋል። ከግሉ ዘርፍ፣ ከትምህርት፣ ከመሰረተ ልማት፣ ከጤና አካታችነት አንጻር ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቅሰው፥ ምክር ቤቱ ለላቀ ስኬት የክትትልና ቁጥጥር ስራውን ማጠናከር እንዳለበት ጠቁመዋል። በአምስተኛው ዓመታዊ የፓርላማ ጥናትና ምርምር ኮንፈረንስ የፓርላማ ዴሞክራሲ ሥርዓት ትግበራ መሻሻል፣የፓርላማ ተግባራትን ማጠናከር፣ የሕግ የበላይት፣አካታች አስተዳደርና ሀገረ መንግሥት ግንባታ ላይ ያተኮሩ 12 የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎች በምሁራን እንደሚቀርቡ የወጣው መርሃ ግብር ያሳያል።
በተለያዩ ሀገራት በችግር ውስጥ የነበሩ ከ131 ሺህ በላይ ዜጎች ተመልሰዋል - የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
Jul 10, 2025 128
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ21 ሀገራት በችግር ወስጥ የነበሩ ከ131 ሺህ በላይ ዜጎች ወደ ሀገራቸው መመለሳቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው ሚኒስቴሩ በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት ዋና ዋና የዲፕሎማሲ ሥራዎችን አስመልክተው ለጋዜጠኞች ማብራሪያ ሰጥተዋል። ኢትዮጵያ በበጀት ዓመቱ ብሔራዊ ጥቅሟን ያስከበሩ የሁለትዮሽና ባለብዙ ወገን ግንኙነት በመፍጠር፣ ቀጣናዊ ትስስር እንዲሁም አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ትብብርን ማጠናከር የሚያስችሉ ስኬታማ የዲፕሎማሲ ስራዎች አከናውናለች ብለዋል። ኢትዮጵያ ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት የበለጠ ማጠናከር የሚያስችሉና ቀጣናዊ ትስስርን የሚያፋጥኑ ፍሬያማ የዲፕሎማሲ ተግባራትን ማከናወኗንም አመልክተዋል። ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ጋር ተያይዞ የኢትዮጵያን እውነት ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ለማስረዳት ጠንካራ የዲፕሎማሲ ሥራዎች መከናወናቸውንም አምባሳደሩ አብራርተዋል። የናይል ተፋሰስ ኮሚሽን እንዲቋቋም በማድረግ ኢትዮጵያ የፍትሃዊ ተጠቃሚነት መሻቷን በተግባር አሳይታለች ነው ያሉት። ኢትዮጵያ ከጎረቤቶቿ ጋር የህዝብ ለህዝብ ትስስርን ለማጠናከር ለ968 የተለያዩ ሀገራት ዜጎች የትምህርት እድል መስጠቷንም ቃል አቀባዩ ጨምረው ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም የሚያስከብሩ 11 ስምምነቶች ተፈርመው በፓርላማ መፅደቃቸውንም ነው አምባሳደር ነብያት ጌታቸው የገለጹት። በኢኮኖሚ ዲፕሎማሲም ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ስለ ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያውና ስለኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ በቂ ግንዛቤ በመያዝ ድጋፉን እንዲያጠናክር የሚያደርጉ ስራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። በበጀት ዓመቱ በዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲ በ21 ሀገራት በችግር ውስጥ የነበሩ ከ131ሺህ በላይ ዜጎች ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ መደረጉንም አስታውሰዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበጀት ዓመቱ የዜጎችን ደህንነትና ክብር የማስጠበቅ ሥራን ቀዳሚ ትኩረት ሰጥቶ መስራቱን አመልክተዋል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ኮንፍረንሶችን የማስተናገድ አቅሟ እያደገ መምጣቱን የጠቀሱት አምባሳደሩ፣ በቅርቡም ትላልቅ ዓለም አቀፍ ጉባኤዎች ይካሄዳሉ ብለዋል። ከእነዚህም ውስጥ የተባበሩት መንግስታት ሁለተኛው የሥርዓተ ምግብ ጉባኤ እና ሁለተኛው የአፍሪካ አየር ንብረት ጉባኤ ተጠቃሽ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአሜሪካ የሚገኙ ኢትዮጵያውያን ከተፈቀደላቸው የቪዛ ጊዜ በላይ መቆየት ከፍተኛ ተጠያቂነትን የሚያስከትል በመሆኑ ዜጎች ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባም ነው ቃል አቀባዩ በመግለጫቸው ያሳሰቡት። የኢትዮጵያን ቪዛ አግኝተው የሚመጡ የሌላ ሀገር ዜጎች ከተፈቀደላቸው የቆይታ ጊዜ በላይ መቆየት በሀገሪቱ ህግ መሰረት ቅጣት የሚያሰጥ መሆኑን በመገንዘብ ጥንቃቄ እንደያደርጉም አፅንኦት ሰጥተዋል።
ምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር ስራን በጥናትና ምርምር በመደገፍ ውጤታማ ተግባር እያከናወነ ነው - አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ
Jul 10, 2025 110
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር ስራን በጥናትና ምርምር በመደገፍ ለአካታች ልማት መሳካት የበኩሉን እየተወጣ መሆኑን የምክር ቤቱ አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጹ። አፈ ጉባኤው ይህን ያሉት "አካታችና ጠንካራ የፓርላማ ስርዓት ለሀገር በቀል እውቀትና ቀጣይነት ላለው ልማት" በሚል በተጀመረው አምስተኛው ዓመታዊ የፓርላማ ጥናትና ምርምር ኮንፍረንስ መክፈቻ መርሃ ግብር ላይ ነው። አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ የምርምር ባህልን ማሳደግ ቀጣይነት ላለው እድገት፣ ጠንካራ ምጣኔ ሃብትና ዘላቂ እድገትን ለማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑንም ተናግረዋል። በመሆኑም የምርምር ኮንፍረንሱ ምክር ቤቱ ለሚያወጣቸው ፖሊሲዎች፣ ህጎችና ለሚያደርገው የክትትልና ቁጥጥር ሥራ አስተዋጽኦው ከፍተኛ እንደሆነ አንስተዋል። ምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር፣ የሕዝብ ውክልና እና የፓርላማ ዲፕሎማሲ ሥራዎችን በጥናትና ምርምር የተደገፉ በማድረግ የህዝብን ጥያቄ ለመመለስ እየሰራ ነው ብለዋል። የህዝብ ቅሬታን ከመሰረቱ በጥናትና ምርምር በመለየት በሚወጡ ህጎችና ፖሊሲዎች በማካተት ዘላቂ መፍትሔ እንዲሰጣቸው እያደረገ መሆኑንም ጨምረዋል። ምክር ቤቱ በቀጣይም ከምርምር ተቋማት ጋር ያለውን የትብብር ሥራ አጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል። በአምስተኛው ዓመታዊ የፓርላማ ጥናትና ምርምር ኮንፍረንስ የፓርላማ ዴሞክራሲ ሥርዓት ትግበራ መሻሻል፣ የፓርላማ ተግባራትን ማጠናከር፣ የሕግ የበላይነት፣ አካታች አስተዳደርና ሀገረ መንግሥት ግንባታ ላይ ያተኮሩ 12 የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎች እንደሚቀርቡ የወጣው መርሃ ግብር ያሳያል። በኮንፍረንሱ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከፍተኛ አመራሮች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ኃላፊዎች፣ ምሁራንና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል።
መንግስት በሁሉም መስክ የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ መሰረት የሚጥሉ ውጤታማ ተግባራትን አከናውኗል
Jul 10, 2025 102
ጎንደር፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፡- በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት መንግስት በሁሉም መስክ የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ መሰረት የሚጥሉ ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑ ተገለጸ። "ጠንካራ አደረጃጀት ለሁለንተናዊ ብልፅግና " በሚል መሪ ሃሳብ የብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ የ2017 በጀት ዓመት ግምገማና የ2018 የእቅድ ትውውቅ መድረክ በጎንደር ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡ በግምገማ መድረኩ ላይ የብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ ሃላፊ አቶ ፍቃዱ ተሰማ እንደተናገሩት፤ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት በፓርቲው አመራር ሰጪነት ሀገርን ወደ ብልፅግና የሚያሻግሩና አለም ምስክርነቱን ጭምር የሰጠባቸው ትርጉም ያላቸው ውጤታማ ተግባራት ማከናወን ተችሏል፡፡ የኑሮ ውድነትን በመቀነስ የህዝቡን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል የሚረዱ የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብርና የበጋ መስኖ ስንዴ ልማት ተጠቃሽ የልማት ተግባራት መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ የከተሞችን እድገት ለማፋጠንና የሕዝቡንም የኑሮ ዘይቤ ለማዘመን እንዲቻል በመላ ሀገሪቱ እየተከናወኑ የሚገኙ የኮሪደር ልማት ስራዎች ከተሜነትን በማላበስ አዲስ ተስፋና ብርሃን የፈነጠቁ ፋና ወጊ የልማት ተግባራት መሆናቸውን ለአብነት ጠቅሰዋል፡፡ የዚህ ትውልድ አኩሪ ድልና ታሪክ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብም ስኬት የህዝባችን አይበገሬነትና የፓርቲያችን የአመራር ቁርጠኝነት የታየበት ነው ብለዋል፡፡ የአማራ ክልል እምቅ የተፈጥሮ ሀብት ባለቤትና በኢትዮጵያ ታሪክም ትልቅ አሻራ ያለው ነው ያሉት አቶ ፍቃዱ፤ የክልሉን ሰላም በማፅናት ልማቱን አጠናክሮ ለማስቀጠል አመራሩና ሕዝቡ ተቀናጅተው ያከናወኑዋቸው ተግባራት የሚደነቁ መሆናቸውን አንስተዋል፡፡ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ፓርቲው የሚመራው መንግስት በርካታ ውጤታማ ተግባራት ማከናወኑን ገልጸው፤ ዛሬም እንደ ትናንቱ በሕዝባችን ተሳትፎና በአመራሩ ቁርጠኛ ያልተሻገርናቸውን በድል ለመወጣት መጪው ዓመት በትጋት ለመስራት ቃል የምንገባበት ነው ብለዋል፡፡ በብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ሃላፊ አቶ ፍሰሃ ደሳለኝ በበኩላቸው፤ የአማራ ክልል ትልቅ የመልማትና የማደግ አቅም ያለው የተፈጥሮ ጸጋዎች ባለቤት መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የክልሉ ሰላም በማፅናት የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶችን ለማጠናቀቅ ርብርብ እየተደረገ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡ ብልፅግና ፓርቲ የጠራና ተሻጋሪ ሃሳብ ያለው በመሆኑ ሰላምና ልማትን ለማረጋገጥ እየተጋ እንደሚገኝ ገልጸው፤ ፓርቲው ለሕዝቡ የገባውን ቃል አክብሮ ወደ ተግባር በማሸጋገር በኩል ሕዝባዊ አደራውን ይወጣል ብለዋል፡፡ ጎንደር የብልፅግና ትሩፋቶች ተቋዳሽ ከሆኑ የሀገራችን ቀደምት ከተሞች አንዱ ለመሆን በቅታለች ያሉት ደገሞ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው ናቸው፡፡ በፌደራልና በክልሉ መንግስት በከተማዋ የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች የቀደመ ገናና ስሟንና ታሪኳን ያደሰ ብሎም የኪነ ጥበብና የኪነ ህንጻ አሻራዋን በደማቁ ያጎሉ ተግባራት መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ የፓርቲው የአደረጃጀት ዘርፍ የአፈጻጸም ግምገማ መድረክ ላይ ከሁሉም የሀገሪቱ ክልሎች የተውጣጡ የፓርቲው የአደረጃጃት ዘርፍ አመራሮች በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ። አመራሮቹ በፌደራልና በክልሉ መንግስት እየተከናወኑ የሚገኙ የሌማት ትሩፋት፣ የኮሪደር ልማት፣ የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት እድሳትና የጥገና ስራ እንዲሁም የመገጭ የመስኖና የመጠጥ ውሃ ግድብ ፕሮጀክቶች ትናንት ተዘዋውረው መጎብኘታቸውን በወቅቱ ተገልጿል።
ኢትዮጵያ በበጀት ዓመቱ ብሔራዊ ጥቅሟን የሚያስጠብቁ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ተግባራትን አከናውናለች - የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
Jul 10, 2025 88
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት ብሔራዊ ጥቅሟን የሚያስጠብቁ ጠንካራ የዲፕሎማሲ ተግባራት ማከናወኗን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የሚኒስቴሩ ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው የበጀት ዓመቱን አበይት የዲፕሎማሲ ክንውኖች አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም በበጀት ዓመቱ በሁሉም የዲፕሎማሲ መስኮች የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም የሚያስጠብቁና የሀገርን ገፅታ የሚያስተዋውቁ የዲፕሎሚሲ ስራዎች መከናወናቸውን አስታውቀዋል። ከጎረቤት ሀገራት ጋር በጋራ ተጠቃሚነት ላይ የተመሰረተ ግንኙነትን በኤሌክትሪክ ኃይልና በመንገድ መሰረተ ልማት ይበልጥ የማጠናከርና በአፍሪካ ቀንድ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ስኬታማ ሥራዎች መፈጸማቸውን አብራርተዋል። በበጀት ዓመቱ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ፍትሐዊ ተጠቃሚነትን በተመለከተም የኢትዮጵያን እውነታ ለዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ማስረዳት መቻሉን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ ከተለያዩ ሀገራት ጋር በርካታ የሁለትዮሽና የባለብዙ ወገን ስምምነቶች መደረጋቸውንም ነው ያነሱት። እነዚህ ስምምነቶች የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም የሚያስጠብቁና በዓለም አቀፍ መድረክ ያላትን ተሰሚነትና ተደማጭነት የሚያጎለብቱ ናቸው ብለዋል። በዜጋ ተኮር ዲፕሎማሲም በተለያዩ ሀገራት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ ኢትዮጵያውያንን ጤንነታቸውና ክብራቸው ተጠብቆ ወደ ሀገራቸው እንዲመለሱ መደረጉን ገልጸዋል።
በሀገሪቱ ስኬቶችን ይበልጥ በማጎልበት የብልፅግና ጉዞውን ለማሳካት የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው ቀጥለዋል
Jul 10, 2025 81
ሀዋሳ፤ ሐምሌ 3/2017 (ኢዜአ)፡- በሀገሪቱ በተለያዩ ዘርፎች የተመዘገቡ ስኬቶችን ይበልጥ በማጎልበት የብልፅግና ጉዞውን ለማሳካት የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸው ተገለጸ። የብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ የ2017 በጀት ዓመት እቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2018 እቅድ ላይ የሚመክር የጋራ መድረክ በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ ላይ የብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ሃላፊ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር) እንዳመለከቱት፤ ፓርቲው በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ባከናወናቸው ተግባራት በርካታ ድሎችና ስኬቶች ተመዝግበዋል። ለተመዘገቡ ድሎችና ስኬቶች በአመራሩ፣ በአባላቱና ሕዝቡ ዘንድ የፓርቲውን አስተሳሰብ በማስረጽ የተከናወኑ ሥራዎች ጉልህ መሆናቸውን ገልጸዋል። ሁለተኛው ጉባኤ በተሳካ ሁኔታ መከናወኑንም አንስተዋል። በዚህም ጥልቅ ውይይቶችን በማድረግ አመራሩ ፣ አባሉና ሕዝቡ ድሉን እንዲጋራና ለብልጽግና ጉዞ በጋራ እንዲሰራ የሚያደርግ አቅም መፍጠር መቻሉንም ተናግረዋል። በፓርቲው በተቀረጹ የተለያዩ ኢንሼቲቮች የሕብረተሰቡን ህይወት የሚቀይሩ ተግባራት መከናወናቸው ጠቅሰው፤ የብልፅግና ጉዞውን ለማሳካት የሚያስችሉ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠላቸውን ገልጸዋል። ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የተጀመረው ስራ ውጤት እየተመዘገበበት መሆኑን የጠቀሱት ሃላፊው፤ መልካም አስተዳደር ማስፈን፣ የኑሮ ውድነትን ማርገብ፣ ስራ አጥነት መቀነስና መሰረተ ልማት ዘርፎች ላይ የተከናወኑ ሥራዎች የሕብረተሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያግዙ እንደሆኑም አብራርተዋል። በብልፅግና ፓርቲ የሲዳማ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ አብረሃም ማርሻሎ በበኩላቸው፤ ፓርቲው አዳዲስ ሃሳቦችን በማፍለቅና ወደ ተግባር በመቀየር ያከናወናቸው ተግባራት ተጨባጭ ውጤት ያመጡ ናቸው ብለዋል። የፓርቲው እሳቤዎች፣ የተቀረጹ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች በአመራሩ፣ አባሉና ሕዝቡ ዘንድ ለማስረጽ የፖለቲካና አቅም ግንባታው ዘርፍ በስልጠና የታገዘ ጉልህ ሚና እንዳበረከተም አንሰተዋል። ባለፈው የበጀት ዓመት የተመዘገቡ ስኬቶችን በማስቀጠልና ጉድለቶችን በመለየት ለቀጣይ ጉዞ ውጤታማነት የመድረኩ ሚና ጉልህ መሆኑን ተናግረዋል። ለሶስት ቀናት በሚቆየው መድረክ የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች እየተሳተፉ ሲሆን፤ የመስክ ምልከታም እንደሚካሄድ ይጠበቃል።
ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያን የግብር ስርዓት በማዘመን የገቢ አሰባሰብ አቅምን ለማሳደግ ያግዛል - ቋሚ ኮሚቴው
Jul 9, 2025 128
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያን የግብር ስርዓት በማዘመን የገቢ አሰባሰብ አቅምን ለማሳደግ የሚያግዝ መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አስታወቀ። ቋሚ ኮሚቴው በፌዴራል የገቢ ግብር አዋጅ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጄ በዚሁ ወቅት በቋሚ ኮሚቴው አባላት ለተነሱ ጥያቄዎች የተሰጡት ምላሽና ማብራሪያዎች ግልፅና የተሻለ መረዳት መፍጠር መስቻሉን ተናግረዋል። ማሻሻያው የግብር አከፋፈል ስርዓትን በማዘመን ግልፅነት በተሞላበትና ፍትሃዊነትን በሚያሰፍን መልኩ ማከናወን የሚያስችል በመሆኑ የሚበረታታ ነው ብለዋል። ማሻሻያው መንግስት ያስቀመጠውን አላማ የሚያሳካና በግብር ከፋዩ ዘንድ የተሻለ መረዳት የሚፈጥር መሆኑንም ጠቅሰዋል። በዚህም ቋሚ ኮሚቴው ለውጤታማነቱ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ አብርሃም አለማየሁ(ዶ/ር) በበኩላቸው ረቂቅ አዋጁ በገቢ ዘርፍ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት ምቹ ሁኔታ የሚፈጥር ነው ብለዋል። ዲጂታል ስርዓት ሲዘረጋ ለተገልጋዮች የበለጠ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተው ለዚህም መሰረተ ልማት ከማሟላት አኳያ በቂ ዝግጅት ሊደረግ እንደሚገባ ገልጸዋል። የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ እዮብ ተካልኝ(ዶ/ር) በሰጡት ማብራሪያ ማሻሻያው የታክስ ህጎች እንዲከበሩ ለማድረግና የመንግስትን ገቢ ለማሳደግ አስፈላጊ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡ የረቂቅ አዋጁ ዋነኛ አላማዎች ዝቅተኛ ገቢ ባላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ላይ ያለውን የግብር ጫና መቀነስ፣ የግብር መሰረትን ማስፋት፣ ለአነስተኛ የንግድ እንቅስቃሴዎች ቀላል የግብር አከፋፈል ስርዓት መዘርጋት ናቸው ብለዋል። እንዲሁም ለኢንቨስትመንት የሚደረገውን ጥረት ማገዝ፣ የታክስ ማጭበርበርን መከላከልና ግልጽነት በሚጎድላቸው አንቀጾች ምክንያት የሚደርሱ ውጣ ውረዶችን ለማስቀረት እንደሆነም አክለዋል።
ምርጫ ቦርድ በተለያዩ ጊዜያት ከተካሄዱ ምርጫዎች ተሞክሮ በመውሰድ ማሻሻያዎችን ማቅረቡ ተገቢ ነው - ቋሚ ኮሚቴው
Jul 9, 2025 99
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በተለያዩ ጊዜያት ከተካሄዱ ምርጫዎች ተሞክሮ በመውሰድ ክፍተቶችን መሙላት የሚያስችሉ ማሻሻያዎችን ማቅረቡ ተገቢ መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። ቋሚ ኮሚቴው የኢትዮጵያ የምርጫ፣ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ስነ-ምግባር ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ የአስረጂ መድረክ አካሂዷል። የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ እውነቴ አለነ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በተለያዩ ወቅቶች ከተካሄዱ ምርጫዎች በመነሳትና የውጪ ተሞክሮን በመቀመር የሀገሪቱን የዲሞክራሲ ስርዓት ለማሳደግ የሚያደርገው ጥረት የሚበረታታ ነው። ቦርዱ ረቂቅ አዋጁን ሲያዘጋጅ በኢትዮጵያ አካታች የፖለቲካ አካሄድ እንዲኖር ለማድረግ ከፍ ያሉ ስራዎች ማከናወኑን መረዳታቸውን ጠቅሰዋል። በዋናነትም ለወጣቶች፣ ለአካል ጉዳተኞችና ሴቶች አካታች እንዲሆን የሰጠውን ትኩረት አድንቀዋል። በኢትዮጵያ ያለው አዳጊ ዲሞክራሲ በመሆኑ ፓርቲዎች ስህተት በሚፈጥሩበት ጊዜ ማረም ተገቢ መሆኑን ጠቁመው፤ ሕግና ስርዓትን ለማስከበርም በረቂቅ አዋጁ የተካተቱት ጉዳዮች ተገቢ መሆናቸውን ተናግረዋል። የምርጫ አስፈፃሚዎች ቁጥርን አስመልክቶ እንደየስራ ጫናው ሊሆን እንደሚገባ ያመለከቱት የቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ ከዚህ አኳያ የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ተገቢ እንደሆነ ጠቅሰዋል። ምርጫን በቴክኖሎጂ ለማከናወን በረቂቅ አዋጁ የተቀመጠው ተገቢና አስፈላጊ ከመሆኑ ባለፈ ጊዜውን የዋጀ ነው ብለዋል። ከቅሬታ ሰሚ አኳያም በቀጣይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት የሚደረግበት መሆኑን ነው ሰብሳቢው ያመላከቱት። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወይዘሮ ሜላትወርቅ ሀይሉ በሰጡት ማብራሪያ፤ ረቂቅ አዋጁ በስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫ ወቅት በአፈጻጸም ላይ የታዩ ክፍተቶችን መፍታት የሚያስችል ማሻሻያ መደረጉን ገልፀው፤ በዋናነትም የመራጭነትና የዕጩነት ምዝገባና የእድሜ ሁኔታን ያካተቱ አንቀፆች መካተታቸውን ነው የተናገሩት። ረቂቅ አዋጁ በተሻለ መልኩ አካታች የሆነ አካሄድ እንዲከተል የተደረገ ሲሆን፤ ለሴቶችና ለአካል ጉዳተኞችም ልዩ ትኩረት መስጠቱን አስረድተዋል።
በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተገኙ አበረታች ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው ይቀጥላሉ - አቶ መለስ አለሙ
Jul 9, 2025 107
ሐረር፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፡- በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተገኙ አበረታች ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ በብልፅግና ፓርቲ የዋናው ጽህፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መለስ አለሙ ገለጹ። የፓርቲው የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የ2017 ዕቅድ አፈጻጸም ግምገማና የ2018 እቅድ ተግባቦት መድረክ በሐረር ከተማ መካሄድ ጀምሯል። አቶ መለስ አለሙ እና በብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ጌቱ ወዬሳን ጨምሮ የፓርቲው የወጣቶችና ሴቶች ክንፍ አመራሮችና ሌሎች የፌደራልና የክልል የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ አመራሮች ተገኝተዋል። በመድረኩ የተገኙት አቶ መለስ አለሙ እንዳሉት በ2017 በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፍ አበረታች ሥራዎች ተከናውነዋል። በበጀት ዓመቱ የተገኙትን ጥንካሬዎች በማስቀጠልና የተስተዋሉ ውስንነቶችን በማረም በ2018 በጀት ዓመት የተሻለ ስራ በማከናወን ለውጡን ማስቀጠል ይገባል ብለዋል። የመሃል ዘመን ፈተናን የምንሻገርበትና አዲስ የማንሰራራት ዘመን መባቻ ላይ የምንገኝ በመሆኑ የ2018 እቅድ ከወትሮው የተለየ ያደርገዋል ነው ያሉት። በተለይ በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራትን በ2018 በጀት ዓመትም በላቀ ደረጃ የምንተገብርበት በመሆኑ ከወዲሁ ዝግጅት እና ልምምድ በማድረግ ወደ ባህል ማሻገር ይገባል ብለዋል። መድረኩም አቅም የምንገነባበትና ትምህርት ወስደን ለቀጣይ በጀት ዓመት ዝግጅት የምናደርግበት ነው ሲሉም ገልጸዋል። መድረኩ በክልሎች መዘጋጀቱ በየአካባቢው ያለውን ባህል ለመረዳት፣ ለመቀራረብና ያሉ ጸጋዎችን ለመረዳት እንዲሁም ተሞክሮ ለመቅሰም እንደሆነም ተናግረዋል። በብልጽግና ፓርቲ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ጌቱ ወዬሳ በበኩላቸው በክልሉ በዴሞክራሲ ባህል ግንባታ የተከናወኑ ተግባራት የሴቶችና የወጣቶች ክንፍ እንዲጠናከር እንዲሁም ከሲቪል ማህበራት ጋር ተቀራርቦ የመስራት ተሞክሮን አስፍቷል ብለዋል። በተለይም ከተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር የነበረውን የተራራቀ አመለካከት በመቅረፍ በልማትና በሰላም ሥራዎች ላይ ተቀራርቦ የመስራት ባህልን አስፍቷል ነው ያሉት። ለሁለት ቀናት በሚቆየው መድረክ የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ የ2017 እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት እና የ2018 መነሻ እቅድ ቀርቦ ውይይት ከተካሄደ በኋላ ለቀጣይ አቅጣጫ ይቀመጣል ተብሎ ይጠበቃል። ከመድረኩ ጎን ለጎን በሐረር ከተማ የተከናወኑ የልማት ስራዎች ጉብኝት እና የችግኝ ተከላ መርሀግብር እንደሚከናወን ተመላክቷል።
ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ የሥራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁትን የተመድ የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ አሰናበቱ
Jul 9, 2025 108
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ የሥራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁትን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ረዳት ዋና ፀሐፊ እና በኢትዮጵያ የድርጅቱ የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ራሚዝ አላክባሮቭን(ዶ/ር) አሰናበቱ። ፕሬዝዳንት ታዬ በዚሁ ወቅት ዶክተር ራሚዝ አላክባሮቭ በስራ ዘመናቸው ላበረከቱት አስተዋፅኦና የተመድ ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማሳካት ላሳዩት ቁርጠኝነት አድናቆትና ምስጋና አቅርበዋል። ዶክተር ራሚዝ ኢትዮጵያ እና የመንግስታቱ ድርጅት ስኬታማ ትብብር እንዲኖራቸው ማድረጋቸውን ያወሱት ፕሬዝዳንቱ፥ በቀጣይ ተልዕኳቸው ስኬታማ እንዲሆን መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል። የተመድ ረዳት ዋና ጸሐፊ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ዶክተር ራሚዝ አላክባሮቭ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ በኢትዮጵያ ትርጉም ያለው ጊዜ ማሳለፋቸውን ገልጸዋል፡፡ በኢትዮጵያ የአረንጓዴ ዐሻራ መርሃ ግብር፣ የከተማ እና የገጠር የኮሪደር ልማት እንዲሁም ሌሎች የለውጥ ሥራዎች አስደናቂ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ዶክተር ራሚዝ አላክባሮቭ ጨምረውም በስራ ዘመናቸው ኢትዮጵያ እና ተመድ የልማት ትብብራቸውን ማጠናከራቸውን ገልጸዋል። ለአብነትም የዘላቂ ልማት ግቦችን ማዕከል ያደረገ የ5 ዓመታት የትብብር ማዕቀፍ መፈረሙን አውስተው፥ ኢትዮጵያ የማይበገር የምግብ ስርዓት ለመገንባት የጀመረችውን ጥረት የሚያጠናክር እንደሆነ ጠቁመዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያና የተመድ ትብብር ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የበኩላቸውን ሚና እንደሚወጡም አረጋግጠዋል፡፡
በኢትዮጵያ እየተከናወነ ያለው የአረንጓዴ ዐሻራ መርኃ ግብር አስደማሚ ለውጥ የታየበት ነው - ተመድ
Jul 9, 2025 133
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ እየተከናወነ ያለው በአለም ትልቁ የሆነው የአረንጓዴ ዐሻራ መርኃ ግብር አስደማሚ ለውጥ የታየበት ነው ሲሉ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ረዳት ዋና ጸሀፊ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ራሚዝ አላካባሮቭ(ዶ/ር) ገለጹ፡፡ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀስላሴ የስራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁትን የተመድ ረዳት ዋና ጸሀፊ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ራሚዝ አላካባሮቭ(ዶ/ር)ን አሰናብተዋል፡፡ በዚህ ወቅት ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀስላሴ በተመድ ረዳት ዋና ጸሀፊው የስራ ዘመን ኢትዮጵያ ከመንግስታቱ ድርጅት ጋር ስኬታማ የሚባል ትብብር እንደነበራት ገልጸዋል፡፡ በውይይታቸውም በኢትዮጵያ እና በተመድ መካከል የቆየው መልካም ትብብር ተጠናክሮ በሚቀጥልበት ሁኔታ ላይ መምከራቸው ተመላክቷል፡፡ የተመድ ረዳት ዋና ጸሀፊ እንዲሁም በኢትዮጵያ የሰብዓዊ ድጋፍ አስተባባሪ ራሚዝ አላካባሮቭ(ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ ባለፉት 2 ዓመታት በኢትዮጵያ አስደናቂ ለውጦችን ተመልክቻለሁ ብለዋል። በኢትዮጵያ ትርጉም ያለው ጊዜ ማሳለፋቸውን ጠቁመው በተለይ በኢትዮጵያ በከተማ እና በገጠር እየተከናወነ ባለው ሰፊ የለውጥ ስራ መደነቃቸውን ተናግረዋል፡፡ በከተሞች የኮሪደር ልማት ፕሮጀክት አማካኝነት አዲስ አበባ እና ሌሎች የክልል ከተሞች እየተቀየሩ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ሌላው አስደማሚ ለውጥ ደግሞ በኢትዮጵያ እየተከናወነ ያለው በአለም ትልቁ የሆነው የአረንጓዴ ዐሻራ መርኃ ግብር መሆኑን አንስተዋል፡፡ በቢሊዮን የሚቆጠር ችግኝ የሚተክል ሀገር አላየሁም ያሉት ምክትል ዋና ጸሀፊው ኢትዮጵያ ቀጣይነት ያለው የልማት ግብን በማሳካት ረገድ ረጅም ርቀት ተጉዛለች ብለዋል። ዶክተር ራሚዝ አላካባሮቭ ጨምረውም በቀጣይም በኢትዮጵያ እና በተመድ መካከል ትብብሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡ ከሳምንታት በፊት የተፈረመው የስድስት ቢሊዮን ዶላር የትብብር ስምምነት በቀጣይ አምስት አመታት የኢትዮጵያን ትላልቅ የልማት ዕቅዶች በመደገፍ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወትም ገልጸዋል፡፡
ተቋማት በጥናት የቀረቡ የፖሊሲ ምክረ ሀሳቦችን ወደ ተግባር መቀየር ይገባቸዋል- የምክር ቤቱ አመራሮች
Jul 9, 2025 105
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ ተቋማት በጥናት የቀረቡ የፖሊሲ ምክረ ሀሳቦችን ወደ ተግባር መቀየር እንደሚገባቸው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አመራሮች ገለጹ። የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አመራርና አባላት ጋር ባካሄደው የምክክር መድረክ የተለያዩ የጥናትና ምርምር ውጤቶች ቀርበው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል። የውይይቱ ተሳታፊ የምክር ቤቱ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዎች መድረኩ በፖሊሲ ዙሪያ ሰፊ ግንዛቤ የተፈጠረበት መሆኑን ገልጸዋል። ኢንስቲትዩቱ እያከናወናቸው ባሉ ስራዎች እና በቀረቡ የምርምር ስራዎች ዙሪያ አስተያየት እና ጥያቄዎችን አንስተዋል። የከተማ፣ መሰረተ ልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መሀመድ አብዶ የምርምር ስራዎቹ ችግር ፈቺ መሆናቸውን በማንሳት፥ ግኝቶቹን ተቋማት እንዲተገብሯቸው ምን እየተሰራ ነው ብለዋል። የጤና፣ ማህበራዊ፣ ባህልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወርቀሰሙ ማሞ፥ ኢንስትዩቱ ትልቅ ሀገራዊ አቅም በመሆኑ ተቋማዊ ብቃትን ለማሳደግ የሰው ኃይል ግንባታ ላይ ትኩረት እንዲሰጥ ጠቁመዋል። ኢትዮጵያን በፖሊሲ ጥናት ተወዳዳሪ ለማድረግ እየተከናወኑ ያሉ የአደረጃጀት ሥራዎች ላይ ማብራሪያ የጠየቁት ደግሞ የመንግስት የልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ኢንጂነር ስለሺ ኮሬ (ዶ/ር) ናቸው። የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፍቃዱ ጸጋ የመንግሥት ተቋማት የሚሰሩ የምርምር ስራዎችን እንዲተገብሩ የተለያዩ ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን አንስተዋል። ከዚህም ባለፈ የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን በሁሉም ሚኒስቴሮች የጥናትና ምርምር የሥራ ክፍሎችን ማቋቋሙን በማንሳት፥ ኢንስቲትዩቱ የጋራ ፎረም በመፍጠር የአቅም ግንባታ ድጋፍ እንደሚሰጥ ገልጸዋል። በ2018 ዓ.ም የፖሊሲ ምርምር የሚመራበትን እና የምርምር የትኩረት መስኮችን ከወዲሁ በአጀንዳ በመቅረጽ ወደ ትግበራ ለመግባት ዝግጅት መደረጉንም ጠቁመዋል። የፕላን እና ልማት ሚኒስትር ዴኤታ በረከት ፍስሐጽዮን በበኩላቸው፥ ኢንስቲቲዩቱ ትልልቅ ተጽእኖ ፈጣሪ የምርምር ውጤቶችን እያበረከተ መሆኑን አንስተዋል። ተቋሙ የፖሊሲ አጀንዳዎችን በመቅረጽ፣ የተፅዕኖ ግምገማ እና የአቅም ግንባታ ስራዎችን በመተግበር ጉልህ ሚና እየተጫወተ ነው ብለዋል። ተቋሙ ከተሰጠው ሀገራዊ ተልእኮ አንጻር እያከናወናቸው ያሉ ስራዎችን አጠናክሮ እንዲቀጥል ምክር ቤቱ ድጋፍ እንዲያደርግ ጠይቀዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር መሰረት ኃይሌ በበኩላቸው፥ የኢንስቲትዩቱ የጥናት ግኝቶች ለፖሊሲዎች ዝግጅት እና ምክር ቤቱ ለሚያጸድቃቸው አዋጆች ተጨማሪ አቅም እየፈጠሩ መሆኑን ገልጸዋል። የተጠኑ የምርምር ውጤቶች ተግባራዊ መደረጋቸውን መከታተል እና መፈተሽ እንደሚገባም አፅንኦት ሰጥተዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሜቴ ሰብሳቢ ደሳለኝ ወዳጆ፥ የምርምር ተቋማት የሚያወጧቸው ምክር ሀሳቦች ለተቋማት ተደራሽ እየተደረጉ መሆናቸው የሚበረታታ ነው ብለዋል። የመንግሥት ተቋማትም በጥናት ላይ ተመስርተው የቀረቡ የፖሊሲ ምክረ ሀሳቦችን ወደ ተግባር መቀየር እንደሚገባቸው አስንገዝበዋል፡፡ ለዚህም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የፖሊሲ ምርምር ኢንስቲትዩት ክትትል የማድረግ ኃላፊነት አለባቸው ነው ያሉት። በመድረኩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ሎሚ በዶን ጨምሮ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢዎች፣ ምክትል ሰብሳቢዎች፣ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች እና ባለድርሻ አካላት ታድመዋል።
ኢጋድ ለደቡብ ሱዳን የነጻነት ቀን የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክቱን አስተላለፈ
Jul 9, 2025 100
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካ የልማት በይነ መንግስታት ባለስልጣን (ኢጋድ) የደቡብ ሱዳን 14ኛ ዓመት የነጻነት ቀን አስመልክቶ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፏል። የኢጋድ ዋና ፀሐፊ ወርቅነህ ገበየሁ (ዶ/ር) ለደቡብ ሱዳን ህዝብ እና መንግስት እንኳን ለነጻነት ቀናችሁ አደረሳችሁ ለማለት እወዳለሁ ብለዋል። ይህ ቀን በፈተናዎች ያልተበገረችው እና የኩሩዋ ሀገር የተስፋ ቃል ኪዳን የተበሰረበት ነው ሲሉ ገልጸዋል። ኢጋድ ለደቡብ ሱዳን ሰላም፣ አንድነት እና ልማት መረጋገጥ ቁርጠኛ እንደሆነ ገልጸው ለሰላም ስምምነቱ ሙሉ ትግበራ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። የነጻነት በዓሉን በጋራ በምናከብርበት የዛሬዋ ዕለት ኢጋድ ከደቡብ ሱዳን ጋር ያለውን አጋርነት ዳግም ያረጋግጣል ነው ያሉት ዋና ፀሐፊው በመልዕክታቸው።
በምግብ ራስን ለመቻል በሚደረገው ጥረት ኮሞሮስ ከኢትዮጵያ ብዙ ልምድ መውሰድ ትችላለች-ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀስላሴ
Jul 8, 2025 171
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦በምግብ ራስን ለመቻል በሚደረገው ጥረት ኮሞሮስ ከኢትዮጵያ ብዙ ልምድ መውሰድ ትችላለች ሲሉ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀስላሴ ተናገሩ። ኮሞሮስ ባቀረበችው ግብዣ መሰረት የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀስላሴ 50ኛው የኮሞሮስ የነፃነት በዓል በሞሮኒ ከተማ ሲከበር መታደማቸው የሚታወስ ነው፡፡ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀስላሴ ከኮሞሮስ ለቀረበላቸው ግብዣ ምስጋና አቅርበው፥ ኢትዮጵያ ከኮሞሮስ ጋር ያላትን የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ የማሸጋገር ፍላጎት እንዳላት አብራርተዋል፡፡ ከ120 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ያላት ኢትዮጵያ በምግብ ምርት ራሷን ለመቻል ባደረገችው ጥረት ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቷንም አስገንዝበዋል። ፕሬዝዳንቱ አክለውም፥ ኮሞሮስ በግብርናው ዘርፍ ከኢትዮጵያ ትልቅ ተሞክሮ ልትወስድ እንደምትችል አስረድተዋል፡፡ የኮሞሮስ ፕሬዝዳንት አዛሊ አሱማኒ በበኩላቸው፥ የፕሬዝዳንት ታዬ በዚህ በዓል ላይ መገኘት ኢትዮጵያ ለኮሞሮስ ያላትን ክብር የሚያሳይ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ፕሬዝዳንት አዛሊ አሱማኒ፥ ከፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀስላሴ ጋር በሁለትዮሽ ጉዳዮች ዙሪያ ፍሬያማ ውይይትን ማድረጋቸውን ጠቁመዋል።፡ በውይይታቸው ወቅትም ኢትዮጵያ የአፍሪካ ማዕከል መሆኗንም ገልጸዋል፡፡ ፕሬዝዳንት አዛሊ ኢትዮጵያ እያስመዘገበች ያለው ኢኮኖሚያዊ ለውጥ አፍሪካውያንን ለተሻለ እድገት የሚያነሳሳ ስለመሆኑም ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ ለውጥ ማሳያ የሆነውን የኢትዮጵያ አየር መንገድም ኮሞሮስን ከተቀረው አፍሪካ እና አለም ጋር በማገናኘት ረገድ ቁልፍ ሚና እየተጫወተ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡ የኮሞሮስ ፕሬዝዳንት አዛሊ አሱማኒ፥ ከኢትዮጵያ ስንዴ የመግዛት ፍላጎት እንዳላትም ተናግረዋል፡፡