ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
በትጥቅ የሚደረግን የጥፋት መንገድ በማስቀረት በንግግር ዘላቂ ሰላም ለመፍጠር በመንግስት እየተደረገ ያለው ጥረት የሚደነቅ ነው
Apr 30, 2025 49
ጎንደር፤ሚያዚያ 22/2017(ኢዜአ)፦በትጥቅ የሚደረግን የጥፋት መንገድ በማስቀረት በንግግር ዘላቂ ሰላም ለመፍጠር በመንግስት እየተደረገ ያለው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን በምእራብ ጎንደር ዞን የገንዳ ውሃ ከተማ አስተዳደር የመንግስት ሰራተኞች ተናገሩ። በገንዳ ውኃ ከተማ አስተዳደር "የጥፋት ክንዶችና መዘዛቸው" በሚል መሪ ሃሳብ ከመንግሥት ሰራተኞች ጋር የምክክር መድረክ ተካሄዷል። ከመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል አቶ አራጋው ፈንታ፤በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ወንጀል እየፈፀመ ያለው ፅንፈኛ ቡድን ብዙ ነገሮችን እያስተጓጎለና ሰዎችንም እየጎዳ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም የታጠቁ ቡድኖች የህዝብ የሰላም ስጋት በመሆናቸው በየአካባቢው ብዙዎች ለምሬትና እንግልት ተዳርገናል ያሉት አቶ አራጋው የመንግስት የሰላም ጥሪ በመቀበል ዘላቂ ሰላም እንዲፈጥሩ ጠይቀዋል። የትኛውንም አይነት የፖለቲካ ጥያቄ የሚያነሳ አካል ጠመንጃውን አውርዶ የውይይት አማራጭን እንዲከተል በመንግስት እየቀረበ ላለው ተደጋጋሚ ጥሪም አድናቆታቸውን ገልጸዋል። ሌላኛው የመንግስት ሰራተኛ አቶ ያዜ ሽባባው እና ወይዘሮ ወርቄ ዋኘው፤ በህዝብ ላይ ዘረፋ፣ እገታ እና ግድያ እየፈፀሙ ያሉ የታጠቁ የጥፋት ቡድኖችን ከጸጥታ ሃይሉ ጎን በመሆን በጋራ መታገል አለብን ብለዋል። የጥፋት አማራጭን በመከተል በህዝብ ላይ በደል እየፈፀመ ያለ ፅንፈኛ ቡድን ከድርጊቱ እንዲታቀብና የመንግስትን የሰላም ጥሪ እንዲቀበልም ጠይቀዋል። የገንዳ ውኃ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አብዱልከሪም ሙሀመድ፤የህዝብና የመንግስት ትብብር በተጠናከረ መልኩ ከቀጠለ የማይፈታ ችግር የማይጋለጥና ተጠያቂ የማይሆን ወንጀለኛ አይኖርም ብለዋል። በመሆኑም የከተማዋን ብሎም የአካባቢውን ሰላም በጋራ በማስጠበቅ ልማታችንን ለማስቀጠል ጥረታችን ይቀጥላል ሲሉ አረጋግጠዋል። በዚህ ረገድ በተለይም የመንግስት ሰራተኛው ድርብ ሃላፊነት ያለው መሆኑን አንስተው፥ ለሰላምና ልማት እጅ ለእጅ ተያይዘን መስራት ይገባናል ብለዋል።
በክልሉ ዘላቂ ሰላምን በማስፈን የልማት ስራዎችን ለማፋጠን የወጣቶች ሚና የጎላ ነው
Apr 30, 2025 52
ደብረ ማርቆስ፤ሚያዚያ 22/2017 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ዘላቂ ሰላምን በማስፈን የልማት ስራዎችን አጠናክሮ ለማስቀጠል በሚደረገው ጥረት የወጣቶች ሚና የጎላ መሆኑ ተገለፀ። በደብረ ማርቆስ ከተማ ከቴክኒክና ሙያ ተማሪዎች ጋር በዘላቂ ሰላም ግንባታ ዙሪያ የውይይት መድረክ ተካሄዷል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር ጽህፈት ቤት የኢኮኖሚ ክላስተር አማካሪ አቶ አስናቀ ይርጉ እንዳሉት፤ ወጣቱ የአገር ተረካቢነት ሚናውን ለመወጣት ለሰላም ዘብ መቆም አለበት። በተለይም የክልሉን ህዝብ አላስፈላጊ ዋጋ እያስከፈሉ ያሉ ሃይሎች ችግርን በመፍጠር ተማሪዎችን ከትምህርት ገበታ ውጪ ማድረጋቸው፣ ሰብዓዊ፣ማህበራዊ እና ቁሳዊ እንዲሁም ኢኮኖሚያዊ ውድመት ማድረሳቸውን አስገንዝበዋል። ስለሆነም እነዚህን ኃይሎች በመታገል አሁን የተገኘውን ሰላም ዘላቂ በማድረግ የድርሻቸውን መወጣት እንደሚጠበቅባቸውም አመልክተዋል። የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መልካሙ ሽባባው በበኩላቸው፥ ከሁሉም የማህበረሰብ ክፍል ጋር በተደረገ ተደጋጋሚ ውይይት በከተማዋ ሰላም እንዲረጋገጥ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ጠቁመዋል። ይህንን ሰላም በማዝለቅም በየአካባቢው የተጀመሩ የመሰረተ ልማት ግንባታ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። ለውጤታማነቱም ወጣቶች ጉልህ ሚናቸውን በማበርከት ለከተማቸው ሰላም ዘብ መሆን እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። በከተማው በተደረገው ውይይት የተሳተፉ የቴክኒክና ሙያ ተማሪዎችም የመማር ማስተማር ስራው ስኬታማ እንዲሆን ለሰላም የድርሻቸውን እንደሚወጡም ተናግረዋል። ''የጥፋት እጆች እና መዘዞቹ" በሚል መሪ ሃሳብ በተካሄደው የውይይት መድረክም የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ተማሪዎችና የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ተገኝተዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት የተለያዩ ሹመቶችን አጸደቀ
Apr 30, 2025 127
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2017(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው መደበኛ ጉባኤው የተለያዩ ሹመቶችን አጽድቋል። ምክር ቤቱ 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ስብሰባውን አካሂዷል። ምክር ቤቱ ባካሄደው መደበኛ ጉባኤ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ የቀረቡለትን የስራ ሃላፊዎች ሹመት አጽድቋል። በዚህም መሰረት፦ 1/ ወይዘሮ ቆንጂት ደበላ ኦላ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሴቶች ህፃናትና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊ፣ 2/ አቶ አወሌ መሐመድ ኡመር የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ ኃላፊ፣ 3/ ወይዘሮ አይሻ መሐመድ አደም የአዲስ አበባ ከተማ የኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር እንዲሁም 4/ ሕይወት ሳሙኤል ጸጋዬ(ኢ/ር) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የግንባታ እና ቁጥጥር ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር በመሆን ተሹመዋል።
የደቡብ ንፍቀ ዓለም ለዓለም የጋራ ደህንነት እና ብልፅግና በትብብር መስራት አለበት - ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር)
Apr 30, 2025 74
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 22/2017(ኢዜአ)፦ የደቡብ ንፍቀ ዓለም ለዓለም የጋራ ደህንነት እና ብልፅግና መረጋገጥ በትብብር መስራት እንዳለበት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ገለጹ። በብራዚል ሪዮ ዴ ጄኔሮ ሲካሄድ የነበረው የ2025 የመጀመሪያ የብሪክስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ ተጠናቋል። በስብሰባው ላይ "የደቡብ ንፍቀ ዓለም የባለ ብዝሃ ወገን ትብብርን በማጠናከር ያለው ሚና" በሚል ርዕስ የተዘጋጀ ውይይት ተካሂዷል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት የደቡቡ የዓለም ክፍል ገለልተኝነትን በማራመድ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት መመስረቻ ቻርተር ውጤታማ በሆነ ሁኔታ እንዲተገበር በመስራት፣ ቅኝ ግዛትን በመታገልና ግጭቶች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ጉልህ ሚና ተጫውቷል። በሀገራት መካከል የወዳጅነት ትብብር እንዲኖር፣ የመልማት መብት እንዲከበር አልፎም ለዓለም ሰላም እና ደህንነት መጠበቅ የተወጣውን ሚና አንስተዋል። የዓለም የአስተዳደር ስርዓትን በከፍተኛ ሁኔታ እየፈተነ ያለውን የፖለቲካ ቀውስ አስመልክቶ በሰጡት አስተያየት የደቡብ ንፍቀ ዓለም ትብብሩን የበለጠ በማጠናከር ለዓለም የጋራ ደህንነትና ብልፅግና መስራት እንዳለበት ተናግረዋል። የደቡቡ ዓለም ከተቀረው ዓለም ጋር ሲነጻጻር በግብርና፣ በኢነርጂ ልማት፣ በቴክኖሎጂ፣ በኢንፎርሜሽንና ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ(አይሲቲ)፣ በመከላከያ፣ በንግድ እና ትስስር ያለውን አቅሞች እና እድሎች በመጠቀም ለደቡብ ንፍቀ ዓለም የጋራ ግብ እውን መሆን መስራት እንደሚገባ አመልክተዋል። በዓለም ላይ ያሉ ተፎካካሪ ፍላጎቶችን በአጋርነት መንፈስ ማስታረቅ እና ዓለም እያስተናገደቻቸው ያሉ ጉዳቶች እንዴት ምላሽ ያግኙ? ለሚሉ ጥያቄዎችም ጽኑ ቁርጠኝነት መያዝ እንደሚያስፈልግ ነው ያነሱት። ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ(ዶ/ር) ከስብሰባው ጎን ለጎን ከቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ዪ ጋር ተወያይተዋል። በውይይቱ ሁለቱ ሚኒስትሮች የሀገራቱን የሁለትዮሽ ትብብር በተለይም የኢኮኖሚ እና ንግድ ትስስር የበለጠ ማጠናከር እንደሚገባ አንስተዋል። ሀገራቱ በባለብዝሃ ወገን መድረኮች ያላቸውን መደበኛ ምክክሮች ለማጠናከርም ተስማምተዋል። በተጨማሪም ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ከተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስትር ሬም አል ሃሺሚ እና ከታይላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማሪስ ሳንጊያምቦንግሳ ጋር ተወያይተዋል። በውይይታቸውም የጋራ ፍላጎቶች በሆኑ መስኮች ላይ የሁለትዮሽ ትብብራቸውን የማስፋት እና ትስስራቸውን የሚያጠናክሩ ኢኒሼቲቮችን መተግበር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መክረዋል። ሚኒስትሩ ከብራዚል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማውሮ ቪዬራ እና ከሩሲያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ ጋር መወያየታቸው ይታወቃል። በብሪክስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ አጋር ሀገራት የሆኑት የቤላሩስ፣ ቦሊቪያ፣ ኩባ፣ ካዛኪስታን፣ ማሌዢያ፣ ናይጄሪያ፣ ታይላንድ፣ ኡዝቤኪስታንና ዩጋንዳ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች መሳተፋቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
አሰባሳቢ እና ገዥ ትርክትን ለማስረጽ በሚደረገው ጥረት የትምህርት ተቋማት ሚናቸውን ማጣናከር ይጠበቅባቸዋል - ማዕከሉ
Apr 29, 2025 91
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ አሰባሳቢ እና ገዥ ትርክትን ለማስረጽ በሚደረገው ጥረት የትምህርት ተቋማት ሚናቸውን ማጣናከር እንደሚጠበቅባቸው የሕገ መንግሥትና ፌደራሊዝም አስተምህሮ ማዕከል ገለጸ። ማዕከሉ "ፌደራሊዝም፣ ህብረ ብሄራዊ ፌደራሊዝም፣ ሀገረ መንግሥት ግንባታና የትምህርት ተቋማት ሚና" በሚል መሪ ሀሳብ ለትምህርት ተቋማት አመራሮች፣ ባለሙያዎችና መምህራን የአሰልጣኞች ሥልጠና መስጠት ጀምሯል። በሥልጠናው ከተለያዩ ክልሎች የተውጣጡ አመራሮችና ባለሙያዎች በመሳተፍ ላይ ሲሆኑ ሥልጠናው ለሁለት ቀናት የሚቆይ ይሆናል። የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር ኃይለየሱስ ታዬ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ ህብረ ብሄራዊ ፌዴራሊዝምና ሀገረ መንግሥት ግንባታ መሳካት ለሀገር ዘላቂ ሠላምና እድገት መረጋገጥ ቁልፍ ሚና አለው። በመሆኑም በትምህርት ተቋማት በኩል ያለውን ግንዛቤ ለማስፋት ጥናት መደረጉን ጠቅሰው፤ በጥናቱ መሰረት የትምህርት ማኀበረሰቡን ወደ ማሰልጠን መገባቱን አብራርተዋል። ተሳታፊዎችም በሥልጠና ቆይታቸው የቀሰሙትን እውቀት በትምህርት ተቋማት ብሎም ማህበረሰቡን በማስገንዘብ የፌደራሊዝም ጽንሰ ሀሳብ እንዲሰርጽ የበኩላቸውን ኃላፊነት ሊወጡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የፌደራሊዝም ጉዳይ በትምህርት ተቋማት በሥርዓተ ትምህርት ተካትተው ለተማሪዎች በአግባቡ እንዲሰጡ ማዕከሉ ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር በቅንጅት እየሰራ ነው ብለዋል። በፌደሬሽን ምክር ቤት የመንግሥታት ግንኙነት ባለሙያ አቶ ዘውዴ ደምሴ በበኩላቸው በኢትዮጵያ አሰባሳቢ እና ገዥ ትርክትን ለማስረጽ በሚደረገው ጥረት የትምህርት ተቋማት ሚናቸውን ሊያጠናክሩ እንደሚገባ ተናግረዋል። በተማሪዎች ዘንድ የአንድነት እሴት እንዲያብብ በክበባት ሀገራዊ አንድነት የሚያጠናክሩ ሀሳቦች እንዲቀነቀኑ፣ ሕገ መንግሥትና ፌደራሊዝም ጉዳዮች ላይ በትኩረት መሥራት እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። ከስልጠናው ተሳታፊዎች መካከል አቶ ተሻለ ታደሰ በሰጡት አስተያየት ሥልጠናው ያለኝን ግንዛቤ በማስፋት ለሌሎች እንዳካፍል ትልቅ ስንቅ ይሆነኛል ሲሉ ገልጸዋል። አቶ ገመቺስ ኦላና በበኩላቸው መሰል የአቅም ግንባታ መርሃ ግብሮች ዜጎች ፌደራሊዝምን በተሻለ መልኩ ተረድተው እንዲተገብሩት አዎንታዊ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።
ምክር ቤቱ የክልሉን ሕዝቦች መብትና ፍትሃዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል - የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት
Apr 29, 2025 66
ቴፒ፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፦ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ብሔረሰቦች ምክር ቤት የክልሉን ሕዝብ መብትና ፍትሀዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን ገለፀ። የምክር ቤቱ ሦስተኛ ዓመት አራተኛ መደበኛ ጉባኤ በቴፒ ከተማ ተካሂዷል። የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ መቱ አኩ በወቅቱ እንዳሉት ምክር ቤቱ የክልሉን ሕዝቦች መብትና ፍትሀዊ ተጠቃሚነት ማረጋገጥ የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነ ነው። የለውጡን መልካም ዕድል በመጠቀም በክልሉ ውስጥ የሚገኙ ብሔረሰቦች መብትና ጥቅም እንዲረጋገጥ፣ በቋንቋ ልማትና በታሪክ ስነዳ ላይ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት እየተሠራ ነው ብለዋል። ባለፉት 9 ወራት በክልሉ ጎጂ ልማዳዊ ድርጊቶችን መከላከል፣ የሰላም እሴት ግንባታና የሀገር በቀል እውቀት ልማት ላይ ያተኮሩ ተግባራት መከናወናቸውን አመላክተዋል። የግጭት አፈታት እሴትን ለማጎልበትም ለተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ስልጠና መሰጠቱን የገለፁት ደግሞ የምክር ቤቱ ምክትል አፈ ጉባኤ አቶ መሰለ ከበደ ናቸው። የስድስት ብሔረሰቦችን ባህላዊ እሴቶች ማጥናት የሚያስችል ሂደት በመጠናቀቅ ላይ መሆኑን ተናግረዋል። ግጭት እንዳይከሰት መከላከል የሚያስችል ውይይት መደረጉን እንዲሁም ችግሮቹ እየተቀረፉ መምጣታቸውንና በቀጣይም ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀራረብ በቅንጅት ይሠራል ብለዋል።
ኢትዮጵያ ከብራዚልና ሩሲያ ጋር ያላትን የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን ትብብር ለማጠናከር እንደምትሰራ ገለጸች
Apr 29, 2025 130
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 21/2017(ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ ከብራዚል እና ሩሲያ ጋር ያላትን የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን ትብብር ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆኗን አስታወቀች። የ2025 የመጀመሪያው የብሪክስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ በብራዚል ሪዮ ዴ ጄኔሮ እየተካሄደ ነው። ኢትዮጵያ በውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮቹ ስብስባ ላይ እየተሳተፈች ይገኛል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ(ዶ/ር) ከስብስባው ጎን ለጎን ከብራዚል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማውሮ ቪዬራ እና ከሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ ጋር ተወያይተዋል። ከቪዬራ ጋር በነበራቸው ውይይት ብራዚል በ2025 የብሪክስ ፕሬዝዳንነቷ እያከናወነች ያለውን ስኬታማ ስራ አድንቀው ኢትዮጵያ ለብራዚል የትኩረት አቅጣጫዎች ድጋፍ እንደምታደርግ አመልክተዋል። ሁለቱ ወገኖች በውይይታቸው ሀገራቱ የምግብ ዋስትና ማረጋገጥ፣ የግብርና ምርታማነት፣ የዓለም የአስተዳደር ተቋማት ሪፎርም፣ የኢነርጂ ሽግግር እና የደን ልማት ፕሮግራሞች በትብብር መስራት በሚቻልባቸው ጉዳይ ላይም መክረዋል። ሚኒስትር ማውሮ ብራዚል እ.አ.አ በ2024 የቡድን 20 ፕሬዝዳንት በነበረችበት ወቅት ስትተገብራቸው የነበሩ ኢኒሼቲቮችን በማንሳት ኢትዮጵያ ላደረገችው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። ኢትዮጵያ የዓለም አቀፉ የፀረ- ረሃብ እና ድህነት ጥምረት ቦርድ አባል በመሆን እያከናወነች ያለውን ስራ በማሳያነት ጠቅሰዋል። በተያያዘም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ(ዶ/ር) ከሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሰርጌ ላቭሮቭ ጋር በነበራቸው ቆይታ የኢትዮጵያ እና ሩሲያ ሁሉን አቀፍ ትብብር እየተጠናከረ መምጣቱን ገልጸው ትስስሩን ወደ ላቀ ደረጃ ማድረስ እንደሚገባ አመልክተዋል። ሰርጌ ላቭሮቭ በበኩላቸው ሩሲያ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ታሪካዊ ግንኙነት በሁለትዮሽ እና በባለብዙ ወገን የትብብር አማራጮች የበለጠ ለማጠናከር ቁርጠኛ እንደሆነች ገልጸዋል። ጌዲዮን ጢሞቴዎስ(ዶ/ር) ከስብሰባው ጎን ለጎን ከብሪክስ አባል ሀገራት አቻዎቻቸው ጋር የሁለትዮሽ ውይይቶችን እንደሚያደርጉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
የአማራ ክልል በተሻለ የሰላምና ልማት ጉዞ ላይ ይገኛል - የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Apr 29, 2025 171
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 21/2017(ኢዜአ)፦የአማራ ክልል ከመቼውም ጊዜ በላይ በተሻለ የሰላምና ልማት ጉዞ ላይ እንደሚገኝ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ተናገሩ። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፥ የክልሉን ወቅታዊ የሰላምና የልማት ጉዳዮች በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። ርዕሰ መስተዳደሩ በዚሁ ጊዜ፤ በክልሉ ተፈጥረው የነበሩ የሰላምና የጸጥታ ችግሮች በዋናነት ከፖለቲካዊ ጽንፈኝነት ጋር የተያያዙ እንደሆኑ አስታውሰው፤ በወቅቱ አመራሩ በሚጠበቅበት ልክ ችግሩን ታግሎ በማስተካከል ረገድ ለዘብተኛ አቋም መውሰዱም ተናግረዋል። በዚህም ጽንፈኛ ቡድኖች በክልሉ ነዋሪዎች ላይ ሰብዓዊ፣ ቁሳዊ፣ ማኅበራዊና ሥነ-ልቦናዊ ጉዳት ማድረሳቸውን ጠቁመዋል። መንግስት በክልሉ ሰላምን በማስፈን ረገድ ማህበረሰቡን በማሳተፍ ውጤታማ ስራ ማከናወኑንም ተናግረዋል። የክልሉ ነዋሪዎችም የጽንፈኛ ቡድኑን ትክክለኛ ማንነት ተገንዝበው ከመንግስት ጎን በመሆን ለዘላቂ ሰላም የበኩላቸውን ሚና እየተወጡ መሆኑንም ጠቅሰዋል። አሁን ላይ ክልሉ ከመቼውም ጊዜ በላይ በተሻለ የሰላምና የልማት ጉዞ ላይ እንደሚገኝም አብራርተዋል። በክልሉ የተገኘውን ሰላም ዘላቂና አስተማማኝ ለማድረግ በመንግሥት በኩል ሁለት የመፍትሄ አቅጣጫዎች መቀመጣቸውን አስረድተዋል። የመጀመሪያው ለሰላም አማራጮች ቅድሚያ ሰጥቶ መስራት መሆኑን ጠቅሰው፤ በዚህ ረገድ መንግስት ዘወትር ለሰላም በሩን ክፍት አድርጎ እየሰራ ነው ብለዋል። በሌላ በኩል የቀረበውን የሰላም ጥሪ ወደ ጎን በመተው የክልሉን ሰላም ለማወክ በሚሰሩ ጽንፈኛ ቡድኖች ላይ መንግስት ሕግ የማስከበር ኃላፊነቱን እየተወጣ እንደሚቀጥል አብራርተዋል። የአማራ ክልል ሕዝብ በቀጣይ ሰላምን በማስጠበቅ በኩል ከመንግስት ጎን በመሆን የጀመረውን ጥረት አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጥሪ አቅርበዋል።
ምክር ቤቱ በዛሬው እለት ስብሰባው የእንስሳት ጤና እና ደህንነት ረቂቅ አዋጅን መርምሮ ያፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል
Apr 29, 2025 110
አዲስ አበባ፤ሚያዚያ 21/2017(ኢዜአ)፦የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 27ኛ መደበኛ ስብሰባውን ዛሬ ያካሂዳል። በዚህም የእንስሳት ጤና እና ደህንነት ረቂቅ አዋጅን አስመልክቶ የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለምክር ቤቱ ሪፖርት እና የውሳኔ ሀሳብ የሚያቀርብ ሲሆን ውይይት ከተደረገበት በኋላ እንደሚፀድቅ ይጠበቃል። በተጨማሪም ምክር ቤቱ የተጓደሉ የቋሚ ኮሚቴ አመራሮችን ለመሰየም የሚቀርብ የውሳኔ ሀሳብ መርምሮ ያጸድቃል ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልጿል።
የዓለም ስርዓት በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት እኩል ውክልናን በሚያረጋግጥ መልኩ ማሻሻያ ሊደረግበት ይገባል - ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር)
Apr 28, 2025 124
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2017(ኢዜአ)፡- የዓለም የአስተዳደር ስርዓት በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት እኩል ውክልናን በሚያረጋግጥ መልኩ ማሻሻያ ሊደረግበት እንደሚገባ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) አመለከቱ። የባለብዝሃ ወገን የዲፕሎማሲ ማዕቀፍ መጠናከር ለሪፎርሙ ቁልፍ ሚና እንደሚኖረውም ገልጸዋል። የ2025 የመጀመሪያው የብሪክስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ስብሰባ ዛሬ በብራዚል ሪዮ ዴ ጄኔሮ መካሄድ ጀምሯል። በውይይቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) እየተሳተፉ ነው። የሚኒስትሮቹ ስብሰባ መክፈቻ ላይ “ብሪክስ የዓለም እና ቀጣናዊ ቀውሶችን ለመፍታት ያለው ሚና፣ ለሰላም እና ደህንነት መረጋጋጥ የሚያስችሉ መንገዶችን ማጠናከር” በሚል ርዕስ የተዘጋጀ ውይይት ተካሂዷል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) በውይይቱ መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያ ለብዝሃ ወገን ትብብር እና የጋራ ደህንነት ያላትን ቁርጠኝነት አረጋግጠዋል። የዓለም አስተዳደር ስርዓት ላይ ማሻሻያ በማድረግ አፍሪካን ጨምሮ በማደግ ላይ የሚገኙ ሀገራት በእኩልነት የሚወከሉበት ስርዓት መፍጠር እንደሚገባም አመልክተዋል። የዓለም አቀፍ ተቋማት ሪፎርም አንኳር ትኩረት የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የባለብዝሃ ወገን ማዕቀፍ ማጠናከር ላይ መሰረት ያደረገ መሆን አለበት ነው ያሉት። ሚኒስትሩ በዓለም ላይ ያሉ ውጥረቶችን አስመልክቶ ሀሳባቸውን ያነሱ ሲሆን የብሪክስ ሀገራት ቀውሶቹ በሰላማዊ እና ዲፕሎማሲያዊ አማራጭ እንዲፈቱ ጥረት እያደረጉ እንደሚገኙ ተናግረዋል። እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች የደቡብ ንፍቀ ዓለምን የደህንነት፣ የኢኮኖሚ እና አጠቃላይ ፍላጎቶችን የሚያስጠብቁ መሆን እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። በስብሰባው በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ በመምከር የጋራ የሚኒስትሮች የአቋም መግለጫን እንደሚያወጣ ይጠበቃል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ከስብሰባው ጎን ለጎን ከብሪክስ አባል ሀገራት አቻዎቻቸው ጋር የሁለትዮሽ ውይይቶችን እንደሚያደርጉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
ሰላም ሚኒስቴር ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን፣ ህብረ ብሄራዊ አንድነትና አብሮነትን ለማጠናከር እያከናወነ ያለው ተግባር የሚደነቅ ነው - ቋሚ ኮሚቴው
Apr 28, 2025 131
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2017(ኢዜአ)፦ ሰላም ሚኒስቴር ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን፣ ህብረ ብሄራዊ አንድነትና አብሮነትን ለማጠናከር እያከናወነ ያለው ተግባር የሚደነቅ መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። ቋሚ ኮሚቴው የሰላም ሚኒስቴርን የ2017 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈፃፀም ገምግሟል። ቋሚ ኮሚቴው ባቀረበው ግብረ መልስ እንዳስታወቀው፤ ሚኒስቴሩ የፌዴራልና የክልል መንግስታትን እንዲሁም የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን ለማጠናከር የሰራቸው ስራዎች የሚደነቁ ናቸው። ሚኒስቴሩ በሀገር ግንባታና ዘላቂ ሰላምን በማስፈን ሊሂቃን ሊያበረክቱት በሚገባ ሚና ላይ ያተኮረ ውይይት በማድረግ የጋራ መግባባት ላይ መድረሱን ተጠቁሟል። የአጋርና የባለድርሻ አካላትን ተሳትፎ በማጠናከር ሚኒስቴሩ እየሰራ መሆኑን ቋሚ ኮሚቴው ጠቁሞ፤ ሀገራዊ አንድነትንና አብሮነትን ለማጎልበት ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች መስራቱን አብራርቷል። ሚኒስቴሩ የተቋሙን ሪፎርም ስራዎች እያከናወነ መሆኑና የተቀናጀ የፋይናንስ አስተዳደር ስርዓትን በመዘርጋት በጀት በአግባቡ መጠቀሙም ተመልክቷል። የሰላም ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ የዘጠኝ ወር ሪፖርቱን ባቀረቡበት ወቅት እንደገለጹት፤ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን ከክልሎች ጋር በመተባበር የተሰራው ስራ ውጤት አስገኝቷል። ለአብነትም በአፋርና ሶማሌ ክልሎች በቅንጅት የተሰራው ስራ ያስመዘገበውን ስኬታማ ውጤት አንስተዋል። ሚኒስቴሩ ብሄራዊ ጥቅም፣ ማንነት፣ ዕሴትና ዘመኑን የዋጀ አርበኝነት ላይ ያተኮሩ አራት ሰነዶች ማዳበር መቻሉን አመልክተዋል። እስከ አሁን በ12 ዙር ከ80ሺህ በላይ የሰላም በጎ ፍቃድ ወጣቶችን በማሰማራት ወጣቶች ህብረ ብሄራዊ አንድነትና ዘላቂ ሰላም ግንባታ ላይ የተለያዩ ስራዎች ማከናወኑም አብራርተዋል። የቋሚ ኮሚቴ አባላት ባቀረቡት ጥያቄና አስተያየት፤ ሚኒስቴሩ ዘላቂ የልማት ግቦች ከሰላም ግንባታ ጋር ለማስተሳሰርና ህብረ ብሄራዊ አንድነትን ለማጎልበት በበጎ ፈቃደኞች በተሰሩ ስራዎች ምን ውጤቶችን እንዳስመዘገበ ጠይቀዋል። የሰላም ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ ለተነሱ ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ ሚኒስቴሩ ብሄራዊ የበጎ ፈቃድ ወጣቶችን በማሰማራት ለህብረ ብሄራዊ አንድነት የሚያበረክተውን አስተዋፅኦ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል። ዘላቂ ሰላም ለማስፈንና ልዩነቶችን ለመፍታት እንዲሁም ለማረም ሀገራዊ ምክክር የኮሚሽንና የሽግግር ፍትህ በኩል ትልልቅ ተግባራት እንደሚከናወኑ ጠቁመዋል። የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዲማ ኖጎ(ዶ/ር) ሚኒስቴሩ የፌዴራልና የክልል መንግስታትን ግንኙነትና የህዝብ ለህዝብ ትስስርን ለማጠናከር የሰራው ስራ የሚበረታታ ነው። የብሄራዊ በጎ ፍቃድ ወጣቶችን በማሰማራት እንዲሁም የአሰራር ስርዓቱን ለማዘመን የሰራው ስራ አበረታች መሆኑንም ጠቁመዋል። ህብረ ብሄራዊ አንድነትና አብሮነትን ለማጠናከር እንዲሁም የቅድመ ግጭት ትንበያ ላይ በጥናት ላይ ተመስርቶ ያከናወነው ስራም ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተናግረዋል። የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ ፈትሂ ማህዲ(ዶ/ር) በበኩላቸው ሚኒስቴሩ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም ማስፈን የሚያስችሉ ውጤታማ ስራዎች ማከናወኑ የሚበረታታ ነው ብለዋል። የፌዴራሊዝም ስርዓትን ለማጠናከርና ግጭቶችን አስቀድሞ መከላከል የሚያስችሉ አበረታች ስራዎች ማከናወኑንም ተናግረዋል። ቋሚ ኮሚቴው ሚኒስቴሩ የግጭት መከላከልና መከታተያ ቴክኖሎጂ ተደራሽ እንዲሆንና ባህላዊ የግጭት አፈታት እሴቶችን ለማስቀጠል በትኩረት እንዲሰራ ጠይቋል።
መዲናዋን ሰላማዊ፣ የተረጋጋች እና ለመኖር ምቹ ማድረግ የሚያስችሉ ውጤታማ የፀጥታ ስራዎች ተከናውነዋል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 28, 2025 103
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2017(ኢዜአ)፡- አዲስ አበባን ሰላማዊ፣ የተረጋጋች እና ለመኖር ምቹ ማድረግ የሚያስችሉ ውጤታማ የፀጥታ ስራዎች መከናወናቸውን የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ከንቲባ አዳነች አቤቤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዘጠኝ ወራት የፀጥታ ስራዎችን ገምግመዋል። በግምገማው ላይ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ተገኝተዋል። ከንቲባዋ የከተማዋን እድገት እና ለውጦች የሚመጥን የፀጥታ መዋቅር ማደራጀት፣ ቅንጅታዊ አሰራር በማጠናከር የፀጥታ ስጋት ሊሆን የሚችሉ እንቅስቃሴዎችን ቀድሞ በመለየትና ህዝቡን በቀጥታ በማሳተፍ የሰላሙ ባለቤት እንዲሆን በተከናወኑ ስራዎች ስኬቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል። ወንጀል በመከላከል፣ ተጠርጣሪዎችን አድኖ በመያዝ በመመርመርና በማስቀጣት ከተማዋን ሰላማዊ፣ የተረጋጋች እና ለመኖር ምቹ በማድረግ ረገድ ውጤቶች መገኘታቸውንም አመልክተዋል። በግምግማው ላይ የፀጥታ መዋቅሩ የከተማ አስተዳደሩ ለፀጥታ አካላት እያደረገ ያለው ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ትልቅ የሞራል ስንቅ እንደሆናቸው መናገራቸውን አመልክተዋል። በከተማዋ የወንጀል መከላከል እና የመቆጣጠር አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱ የከተማው ነዋሪዎች በሰላም ሰራዊት በመደራጀት ያበረከተዉ የላቀ አስተዋፅኦ፣ የሰላም እና የፀጥታ መዋቅር፣ የፓሊስ ኃይል፣ ደንብ ማስከበር እና ሌሎች የፌደራል ፀጥታ አካላት ጋር የመስራቱ ውጤት እንደሆነም በማንሳት። ከንቲባዋ መዲናዋን ከተደራጀ የዝርፊያ፣ ሌብነት፣ ንጥቂያ እና ከየትኛውም የፀጥታ ስጋት የፀዳች በማድረግ፣ ተቋማዊ ብቃት በማሳደግ፣ የሪፎርም ስራን በማጠናከር፣ የአገልጋይነት ስነምግባር በመላበስ ህብረተሰቡን እንደከዚህ ቀደሙ ሁሉ በብቃት ማሳተፍ እንደሚገባ ተናግረዋል። የሰላምና ጸጥታ ቢሮ፣ የአዲስ አበባ ፖሊስ፣ የሰላም ሰራዊት እና የደንብ ማስከበር አባላት ከሌሎች የጸጥታ አካላት ጋር ቅንጅታዊ አሰራርን ይበልጥ በማጠናከር የተገኙ ለውጦችን አጠናክረው እንዲሰሩ ማሳሰባቸውንም የከንቲባ ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።
ለሰላም ግንባታ አዎንታዊ አስተዋጽኦ ያላቸውን ተግባራት ለማስፋት እየተሰራ ነው - ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ
Apr 28, 2025 116
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 20/2017(ኢዜአ)፦ በተለያዩ ተቋማት እየተሰሩ ያሉ ለሰላም አዎንታዊ አስተዋጽኦ ያላቸውን ተግባራት ለማስፋት እየተሰራ መሆኑን የሰላም ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ ገለጹ። የሰላም ሚኒስቴር የ2017 በጀት ዓመት የዘጠኝ ወራት ዕቅድ አፈፃፀም ሪፖርት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ እያቀረበ ይገኛል። በዚህ ወቅት የሰላም ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ እንዳሉት ባለፉት ዘጠኝ ወራት ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደትን ለማጠናከርና ሀገራዊ ገዢ ትርክትን ለመገንባት በትምህርት ቤቶች የሰላም ክበባትን የማጠናከር ስራ ተሰርቷል። በሀገር ግንባታና ዘላቂ ሰላምን በማስፈን ሊሂቃን ሊያበረክቱት በሚገባ ሚና ላይ ያተኮረ ውይይት በማድረግ የጋራ መግባባት ላይ መደረሱን ነው የተናገሩት። ሀገራዊ ጥቅም፣ ማንነት፣ ዕሴትና ዘመኑን የዋጀ አርበኝነት ላይ ያተኮሩ አራት ሰነዶችን ማዳበር መቻሉንም ጠቅሰዋል። እስከአሁን በ12 ዙር ከ80ሺህ በላይ የሰላም በጎ ፍቃድ ወጣቶችን ማሰማራት መቻሉን ገልጸው፤ በዚህም ወጣቶች ህብረ ብሄራዊ አንድነትና ዘላቂ ሰላም ግንባታ ላይ የተለያዩ ስራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል። በተለያዩ ተቋማት እየተሰሩ ያሉ ለሰላም አዎንታዊ አስተዋጽኦ ያላቸውን ተግባራት ሀገራዊ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። ተደጋጋሚ ግጭት የሚፈጠርባቸው አካባቢዎችን በመለየትና ችግሮችን በዘላቂነት መፍታት የሚያስችሉ ስራዎች መከናወናቸውንም አብራርትዋል። ባለፉት ዘጠኝ ወራት ለሰላም ግንባታ አስተዋጽኦ ያላቸው 18 ሚሊየን የማህበረሰብ ክፍሎችን ማወያየት መቻሉንም ገልጸዋል።
የምስራቅ አፍሪካን ስትራቴጂካዊ ቀጣናነት የሚመጥን ጠንካራ የፖሊስ ኃይል መገንባት ያስፈልጋል - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 27, 2025 136
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ የምስራቅ አፍሪካን ስትራቴጂካዊ ቀጣናነት የሚመጥን ጠንካራ የፖሊስ ኃይል መገንባት ያስፈልጋል ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ የተመሰረተበትን 116ኛ ዓመት በማስመልከት አምስተኛው የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር የመክፈቻ መርሃ ግብር በሻምበል አበበ ቢቂላ ስታዲየም ተካሂዷል። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በመክፈቻ ንግግራቸው፤ ኢትዮጵያ የአፍሪካውያን የሺህ ዘመናት የስልጣኔ መገለጫ፣ የነጻነታቸው ፋና ወጊ እንዲሁም የተቋማት ምስረታ ታሪካቸው ማስረጃ ናት ብለዋል። ለዚህም ከ116 ዓመታት በፊት በ1901 ዓ.ም የተመሰረተው የኢትዮጵያ ፖሊስ ሁነኛ ምልክት መሆኑን አውስተዋል። ኢትዮጵያ በአስቸጋሪ ወቅቶች በዓለም አቀፍ መድረኮች ለአፍሪካውያን የተሟገተች ሀገር መሆኗን ገልጸው፤ ከሌሎች አፍሪካውያን ጋር አህጉራዊና ቀጣናዊ የህብረት ድርጅቶችን መመስረቷን ተናግረዋል። የምስራቅ አፍሪካ ህዝቦች የጋራ ታሪክ፣ ቋንቋ፣ ባህልና ርዕይ ያለን ነን ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ የኢትዮጵያ ፖሊስም ከተለያዩ ሀገራት ጋር በወንድማማችነት መንፈስ በትብብር እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም የበርካታ ሀገራትን የፖሊስ ሠራዊት ማሰልጠኑን፣ አንዳንድ ሀገራት የፖሊስ ተቋም እንዲመሰርቱ ድጋፍ ማድረጉንም አውስተዋል። የአፍሪካ ሰላም፣ ዕድገትና ብልፅግና ያለጠንካራ የፖሊስ ተቋማት አይታሰብም ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በስልጠና የዳበረ፣ በቴክኖሎጂ የዘመነ፣ ከዓለም ነባራዊ ሁኔታ ጋር በተናበበ መልኩ የሚጓዝ ብቁ የፖሊስ ኃይል መገንባት የግድ መሆኑንም ነው የገለጹት። የምስራቅ አፍሪካ አካባቢ በእስያና በአፍሪካ አህጉራት መካከል ቁልፍ ቦታ ላይ የሚገኝ መሆኑን በመጥቀስ፤ ጠንካራ የፖሊስ ሠራዊት የሚያስፈልገው ቀጣና መሆኑን ተናግረዋል። ሕጋዊ የሰዎች ዝውውር እና የሸቀጦች ግብይት ለማሳለጥ፣ ቀጣናዊ ሰላምና ደህንነትን ለማረጋገጥ፣ እየረቀቁ የመጡ ወንጀሎችን በጋራ ለመከላከል፣ ዘመናዊ፣ ጠንካራና ዝግጁ የፖሊስ ኃይል ያስፈልጋል ነው ያሉት። ለዚህ ደግሞ በተለያዩ ህብረቶች በኩል በጋራ መስራት እንደሚገባ ጠቅሰው፤ የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅትን ጨምሮ ቀጣናዊ ትብብርን ማጠናከር ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ፖሊስ አደረጃጀቱን እያስተካከለ፣ የአባላቱን የስልጠና ብቃት እያጠናከረ፣ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በመታጠቅ አቅሙን እያዳበረ ዓለም አቀፍ ልምዶችን እያካበተ መምጣቱንም ጠቅሰዋል። ባለፉት ሰባት ዓመታት በጸጥታ ተቋማት የተካሄደው ሪፎርም ፖሊስን ይበልጥ ዘመናዊ፣ ዝግጁ፣ ደረጃውን የጠበቀ፣ ግዳጁን በብቃት የሚወጣ ተቋም እንዲሆን አድርጎታል ነው ያሉት። አፍሪካን በሚመጥን መልኩ ተባብሮ መስራት እንደሚገባ በማንሳት፤ በየአካባቢው ያለንን እውቀት፣ ልምድ፣ ቴክኖሎጂና ብቃት ደምሮ በመጠቀም የተሻለ የፖሊስ ተቋም የመገንባት ህልምን እውን ማድረግ ይቻላል ብለዋል። የምስራቅ አፍሪካ የፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅትም ፖሊሳዊ ህብረትና ወዳጅነትን እንደሚያጠናክር፣ ለአንድ ዓላማ ተቀራርቦ የመሥራት ባህልን እንደሚያዳብር አንስተዋል። የኢትዮጵያ ፖሊስ ኢትዮጵያንና አፍሪካን በዓለም መድረክ ያስጠሩ ስመ ገናና ስፖርተኞችን ማፍራቱንም አውስተዋል። የምስራቅ አፍሪካ ፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅት አባል ሀገራት ስፖርታዊ ውድድር ቀጣናዊ ህብረትን ይበልጥ እንደሚያጠናክርም ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
የአፍሪካውያን ሰላም፣ ዕድገት እና ብልጽግና ያለ ፖሊስ ተቋማት ጥንካሬ እና ብቃት የሚታሰብ አይደለም - ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ
Apr 27, 2025 133
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 19/2017(ኢዜአ)፦ የአፍሪካውያን ሰላም፣ ዕድገት እና ብልጽግና ያለ ፖሊስ ተቋማት ጥንካሬ እና ብቃት የሚታሰብ አይደለም ሲሉ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት ዛሬ የኢትዮጵያ ፖሊስ የተመሰረተበትን 116ኛ ዓመት በዓልን በማስመልከት የሚካሄደውን 5ኛውን የምስራቅ አፍሪካ የፖሊስ አዛዦች ህብረት ድርጅት አባል ሀገራት የስፖርት ውድድር በውቧ አዲስ አበባ በይፋ አስጀምረናል ብለዋል። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ዘመናዊ የፖሊስ ተቋምን ከአንድ ምዕተ ዓመት በፊት በመመስረት ግንባር ቀደምና ተምሳሌት ሀገር ናት ሲሉም ገልጸዋል። ባለፉት ሰባት ዓመታት ያደረግነው የጸጥታ ተቋማት ሪፎርም ደግሞ ፖሊስን ይበልጥ ዘመናዊ፣ ይበልጥ ዝግጁ፣ ይበልጥ ደረጃውን የጠበቀ፣ ይበልጥ ግዳጅ ፈጻሚ እያደረገው ነው ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ ፖሊስ ኢትዮጵያንና አፍሪካን በዓለም መድረክ ያስጠሩ ስመ ጥር ስፖርተኞችን ያፈራ ተቋም ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት አፍሪካዊ የሆኑ ስፖርታዊ ኩነቶችን እንዲያዘጋጅ ታሪኩም ልምዱም ይረዳዋል ሲሉም ገልጸዋል፡፡ አፍሪካውያን አፍሪካን በሚመጥን ደረጃ ተባብረን መሥራት አለብንም ብለዋል፡፡ በየአካባቢያችን ያለንን ዕውቀት፣ ልምድ፣ ቴክኖሎጂና ብቃት ደምረን ከተጠቀምን የተሻለ የፖሊስ ተቋም የመገንባት ሕልማችንን እውን ማድረግ እንችላለን ነው ያሉት፡፡ የምሥራቅ አፍሪካ የፖሊስ አዛዦች ኅብረት ድርጅትም ይሄንን ፖሊሳዊ ኅብረትና ወዳጅነት ያጠናክራል ሲሉም ተናግረዋል። ለአንድ ዓላማ ተቀራርቦ የመሥራት ባህልን ያዳብራል። ይህ የስፖርት ፌስቲቫል ኅብረታችን የበለጠ የሚጠናከርበት እንደሚሆን አምናለሁ ብለዋል በመልዕክታቸው ፡፡ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ በመልዕክታቸው መልካም የውውድር ጊዜ እንዲሆን እመኛለሁ ሲሉም መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል።
ለከተማችን ሰላምና የልማት እቅዶች መሳካት የድርሻችንን ለመወጣት ሁሌም ዝግጁ ነን- የደሴ ከተማ ነዋሪዎች
Apr 26, 2025 164
ደሴ፤ሚያዚያ 18/2017( ኢዜአ)፡-ለከተማችን ሰላምና የልማት እቅዶች መሳካት የድርሻችንን ለመወጣት ሁሌም ዝግጁ ነን ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው የደሴ ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ። የደሴ ከተማ የኮሪደርና ሌሎች ልማቶች ውጤታማ የሆኑት ህብረተሰቡን በማሳተፍ የልማቱም ይሁን የሰላም አጋር መሆኑን በተግባር በማሳየቱ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አስታውቋል። ከደሴ ከተማ ነዋሪዎች መካከል ሸህ ሙስጠፋ አህመድ፤ የሁሉም ነገር መሰረት ሰላም በመሆኑ ሰላምን አስቀድመን የልማት ስራዎችን አስከትለን በቅንጅት በመስራታችን ተጠቃሚዎች ሆነናል ብለዋል። በደሴ ከተማ የተለያዩ የልማት ስራዎች ተጠናክረው የቀጠሉ ሲሆን ኮንፈረንስን ጨምሮ የጎብኝዎች እንቅስቃሴ በመኖሩ ከቱሪዝም ዘርፉ ገቢ እያገኘን ነው ሲሉም ተናግረዋል። በቀጣይም ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት እና የአስተዳደር መዋቅር ጋር በመተባበር ለዘላቂ ሰላምና ልማታችን ዘብ እንቆማለን ሲሉ አረጋግጠዋል። ሌላኛው የከተማዋ ነዋሪ የሆኑት ቀሲስ ዘላለም ቢሆነኝ፤ የእምነት ተቋማትና የኃይማኖት አባቶች የመጀመሪያ ተግባር ሰላምን መስበክና ስለ ሰላም አብዝቶ መጸለይ በመሆኑ በዚሁ መልኩ እያገዝን ነው ብለዋል። ሌላኛዋ የደሴ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ እቴነሽ አባተ፤ የደሴ ከተማ የሰላምና አብሮነት እሴቶች ለሌሎችም ጥሩ ማሳያ የሚሆን ነው ብለዋል። ለከተማችን ሰላምና የልማት እቅዶች መሳካት የድርሻችንን ለመወጣት ሁሌም ዝግጁ ነን በማለት ነዋሪዎቹ አረጋግጠዋል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ሰላምና ደህንነት መምሪያ ሃላፊ ኮማንደር ሰይድ አሊ፤ የደሴ ከተማ አስተማማኝ ሰላም መሰረቶች የህዝቡና የጸጥታ ሃይሉ ጥብቅ ትስስርና መተጋገዝ ያመጣው መሆኑን ገልጸዋል። በየሰፈሩ ነዋሪው ተደራጅቶ ሰላሙን እያስጠበቀና እየተከታተለ መሆኑን ጠቅሰው በዚህም ደሴ ከተማ የትኛውም አካባቢ ወንጀል ፈፃሚዎች በቅጽበት የሚያዙ መሆኑን ጠቅሰው፥ በሁሉም አካባቢ አስተማማኝ ሰላም መኖሩን አረጋግጠዋል። በከተማው በየእለቱ የተለያዩ ሁነቶችና በርካታ ኮንፈረንሶች የሚካሄዱ መሆኑን ገልጸው፥ በዚህም የከተማው ነዋሪ ተጠቃሚ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም የሆቴሎች፣የምግብና መዝናኛ ቤቶች እንዲሁም በሌሎች የአገልግሎት ዘርፍ ላይ የተሰማሩት ሰዎች በእጅጉ ተጠቃሚ ሆነዋል ብለዋል። በመሆኑም የከተማዋን ሰላም በማስጠበቅ ረገድ የወጣቱ፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና አጠቃላይ የነዋሪዎች ተሳትፎ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አስገንዝበዋል።
ሪፎርሙ ገለልተኛ እና ዘመኑን የዋጀ የፀጥታ ተቋም ከመገንባት አንፃር አበረታች ውጤት እያስገኘ ነው- አቶ ኦርዲን በድሪ
Apr 26, 2025 184
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2017 (ኢዜአ)፦ሪፎርሙ ገለልተኛ እና ዘመኑን የዋጀ የፀጥታ ተቋም ከመገንባት አንፃር አበረታች ውጤት እያስገኘ መሆኑን የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ዛሬ በሐረሪ ክልል የሚገኙ የጸጥታ ተቋማት 116ኛው የኢትዮጵያ ፖሊስ የምስረታ በዓልን አስመልክቶ በከተማው የጽዳት ዘመቻ እና አረንጓዴ ስፍራዎችን እንክብካቤ ማካሄዳቸውን በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል። የሪፎርሙ አንዱ አካል የሆነው የተቋም ግንባታ ስራ ብቁ፣ ገለልተኛ እና ዘመኑን የዋጀ የፀጥታ ተቋም ከመገንባት አንፃር አበረታች ውጤት እያስገኘ ነው ብለዋል። በተለይም የክልሉ ፖሊስ ከነበሩበት ዘርፈ ብዙ ችግሮች ተላቆ የፀጥታ እና የህግ ማስከበር ስራዎችን በብቃት ከመፈፀም ባለፈ በዚህ አይነት የልማት ስራዎች መሳየተፉ የሰራዊቱን ህዝባዊነት የሚያመላክት እንደሆነም አመልክተዋል። በቀጣይም የተቋም ግንባታ ስራ ለማጠናከር አስፈላጊውን እገዛ እንደሚደረግ ገልጸው ዛሬ በተካሄደው የልማት ስራ ለተሳተፉ የፀጥታ አመራሮችና አባላት ልባዊ ምስጋና አቅርበዋል።
የኢትዮጵያ አጠቃላይ ኢኮኖሚ በተያዘው ዓመት በታቀደው መሰረት ያድጋል
Apr 26, 2025 186
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 18/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ አጠቃላይ ኢኮኖሚ በተያዘው ዓመት በታቀደው መሰረት በስምንት ነጥብ አራት በመቶ እንደሚያድግ የብልጽግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አስታወቀ። የፓርቲው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ከሚያዚያ 17 እስከ 18 ቀን 2017 ዓ.ም መደበኛ ስብሰባውን ካካሄደ በኋላ መግለጫ አውጥቷል። ለሁለት ቀናት ሲካሔድ የቆየው የብልጽግና ፓርቲ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ተጠናቀቀ በመግለጫውም የኢትዮጵያን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ዲፕሎማሲያዊ ጉዳዮች በዝርዝር መመልከቱን ገልጿል። ኢትዮጵያ በ2018 ከተስፋ ወደ ሚጨበጥ ብርሃን ለመሻገር፤ በ2023 የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት ለመሆን፤ በ2040 ደግሞ ዓለም አቀፍ የብልጽግና አርአያ ለመሆን ያስቀመጠችው ርዕይ እንደሚሳካ የሚያረጋግጡ የስኬት ፍንጮች መታየታቸውን የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው አረጋግጧል፡፡ የስኬት ፍንጮች ፓርቲው የያዘው ፍኖተ ብልጽግና ትክክል መሆኑን እንደሚያመለክትም አትቷል። በኢኮኖሚው ዘርፍ እስከ አሁን ያለው አፈፃፀም የሚያሳየው በያዝነው ዓመት አጠቃላይ ኢኮኖሚው በታቀደው መሠረት በስምንት ነጥብ አራት በመቶ የሚያድግ መሆኑን የሥራ አስፈጻሚው መገምገሙን አረጋግጧል። በዘርፍ ደረጃ ግብርና በስድስት ነጥብ አንድ በመቶ፣ ኢንዱስትሪ በ12 ነጥብ 8 በመቶ፣ ማኑፋክቸሪንግ በ12 በመቶ፣ ኮንስትራክሽን በ12 ነጥብ 3 በመቶ፣ አገልግሎት ደግሞ በሰባት ነጥብ አንድ በመቶ የሚያድጉ መሆናቸው መገምገሙን አመልክቷል። ባለፉት ዘጠኝ ወራት ጠቅላላ የመንግሥት ገቢ ከዓምናው ተመሳሳይ ወቅት አንጻር የ134 በመቶ ብልጫ ማሳየቱንም አመልክቷል። የውጭ ብድር ከጠቅላላ የአገር ውስጥ ምርት ያለው ድርሻ ወደ 13 ነጥብ 7 በመቶ መውረዱን የጠቆመው መግለጫው፤ ለውጭ ገበያ የሚቀርቡት ስድስት ዋና ዋና ምርቶች፣ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸሩ ከ82 በመቶ እስከ 386 በመቶ ጭማሪ ማሳየታቸውን አመልክቷል። በስንዴ፣ በሩዝ፣ በቡና፣ በሻሂ ቅጠል እና በፍራፍሬ ምርቶች በአፍሪካ ቀዳሚ ሆኖ ለመውጣት እየተደረገ ያለው ትግል ፍሬ እያፈራ መሆኑን እንደሚያሳይ መግለጫው አረጋግጧል።
ኢትዮጵያ የአፍሪካ የነፃነት ምልክት ናት - ሌተናል ጄነራል መሐመድ ባሬድ
Apr 26, 2025 142
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 18/2017 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ የአፍሪካ የነፃነት ምልክት ናት ሲሉ የሞሮኮ ሮያል ጦር ኃይል ኢንስፔክተር ጄኔራልና የደቡባዊ ዞን ጦር አዛዥ ሌተናል ጄነራል መሐመድ ባሬድ ገለጹ። ለአፍሪካ ሰላም እና ደህንነት እያደረገች ያለውን ድጋፍ አድንቀዋል። የሞሮኮ ወታደራዊ ልዑካን ቡድን ከመከላከያ ሚኒስቴር የመከላከያ ፋይናንስ ስራ አመራር ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ማርታ ሉዊጂ ጋር ውይይት አድርጓል። የመከላከያ ሚኒስቴር ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሀመድን በመወከል ውይይቱን የመሩት ሚኒስትር ዴኤታዋ ኢትዮጵያ የጋራ ወታደራዊ ጉዳዮች ላይ በትብብር ለመስራት እና የማይቀለበስ ጠንካራ ወታደራዊ ግንኙነት ለመመስረት ዝግጁ መሆኗን ገልጸዋል። ትብብሩን በመከባበር እና በጋራ ፍላጎት ላይ የተመሰረተ ማድረግ እንደሚገባም አመልክተዋል። የሞሮኮ ሮያል ጦር ኃይል ኢንስፔክተር ጄኔራልና የደቡባዊ ዞን ጦር አዛዥ ሌተናል ጄነራል መሐመድ ባሬድ በበኩላቸው፥ ኢትዮጵያ የአፍሪካ የነፃነት ምልክት ናት ብለዋል። በአሁኑ ሰዓትም ለአህጉሪቷ ሰላም እና ደህንነት እያበረከተች ላለው ወታደራዊ ድጋፍ አድናቆታቸውን ገልጸዋል። የሀገራቱ ወታደራዊ ትብብርም ለአፍሪካ ሰላምና ደህንነት የሚጫወተው ሚና ከፍተኛ እንደሆነም አመልክተዋል። በአጠቃላይ የሞሮኮ ልዑካን ቡድን ለኢትዮጵያ እና ለኢትዮጵያ ሰራዊት ያላቸው አክብሮት ታላቅ መሆኑን ተናግረዋል። በውይይቱ ዋነኛ ወታደራዊ፣ሀገራዊ እና አህጉራዊ ትኩረት ናቸው ተብለው በተለዩ የሰላም እና አጠቃላይ ወታደራዊ ጉዳዮች ዙሪያ በጋራ ለመስራት ቁርጠኛ መሆናቸውን የሁለቱም ሀገራት አመራሮች ገልጸዋል። በውይይቱ ላይም የመከላከያ ውጭ ግንኙነት እና ወታደራዊ ትብብር ዋና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሜጀር ጀኔራል ተሾመ ገመቹን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ አመራሮች መገኘታቸውን የመከላከያ ሰራዊት መረጃ ያመለክታል።
ለሁለት ቀናት ሲካሔድ የቆየው የብልጽግና ፓርቲ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ተጠናቀቀ
Apr 26, 2025 204
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 18/2017(ኢዜአ)፦ የብልጽግና ፓርቲ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ለሁለት ቀናት ያካሔደው ጉባኤ ተጠናቋል። የጉባኤውን መጠናቀቅ ተከትሎ የወጣው መግለጫ እንደሚከተለው ይቀርባል፦ ከብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ከሚያዝያ 17 እስከ 18/ 2017 ዓ.ም መደበኛ ስብሰባውን በአዲስ አበባ አካሂዷል፡፡ በዚህ ስብሰባም የኢትዮጵያን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ዲፕሎማሲያዊ ጉዳዮች በዝርዝር ተመልክቷል፡፡ ኢትዮጵያ በ2018 ከተስፋ ወደሚጨበጥ ብርሃን ለመሻገር፤ በ2023 የአፍሪካ የብልጽግና ተምሳሌት ለመሆን፤ በ2040 ደግሞ ዓለም አቀፍ የብልጽግና አርአያ ለመሆን ያስቀመጠችው ርእይ እንደሚሳካ የሚያረጋግጡ የስኬት ፍንጮች መታየታቸውን የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው አረጋግጧል፡፡ እነዚህ የስኬት ፍንጮች የያዝነው ፍኖተ ብልጽግና ትክክል መሆኑን አመላክተውናል፡፡ ከብልፅግና ፓርቲ ሁለተኛ መደበኛ ጉባኤ በኋላ አያሌ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ ስኬቶች ተመዝግበዋል፡፡ ከተለያዩ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በየደረጃው የሚደረገው ምክክርና ትብብር በኢትዮጵያ የፖለቲካ ታሪክ ወደ አዲስ ምእራፍ ገብቷል፡፡ ከአንድ ክልል በስተቀር፣ ለሀገራዊ ምክክር አጀንዳ የማሰባሰብ ምእራፍ በሁሉም ክልሎች ተጠናቅቋል፡፡ በሀገሪቱ የጸጥታ ችግር በነበረባቸው አንዳንድ አካባቢዎችም ሰላም እየሰፈነ ነው፡፡ መንግስት በተደጋጋሚ ያቀረበውን የሰላም ጥሪ ተከትሎ እጅ የሚሰጡና ወደ ሰላም ድርድር የሚመጡ ታጣቂዎች ከዕለት ወደ ዕለት ቁጥራቸው እየጨመረ ይገኛል፡፡ የመንግሥት ሕግ የማስከበርና የማድረግ ዐቅም እየጎለበተ መጥቷል፡፡ ከሶማሊያ ጋር ተፈጥሮ የነበረው ውዝግብ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ተፈትቷል፡፡ ኢትዮጵያ የባሕር በር እንዲኖራት የተያዘው አቋም ዓለም አቀፋዊ ተቀባይነቱ እየጨመረ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ተቋማት ጋር ያላት ግንኙነት ከመሻሻሉም በላይ የሚደረግላት ድጋፍ እያደገ ነው፡፡ በዓለም አቀፍ መድረክ የኢትዮጵያ ተፈላጊነት ጨምሯል፡፡ የዲፕሎማሲ ግንኙነቷም በሁሉም አቅጣጫ ከፍ ብሏል፡፡ እስከአሁን ያለው አፈፃፀም የሚያሳየው በያዝነው አመት አጠቃላይ ኢኮኖሚው በታቀደው መሠረት በ8.4 በመቶ የሚያድግ መሆኑን የሥራ አስፈጻሚው ገምግሟል፡፡ በዘርፍ ደረጃ ደግሞ ግብርና በ6.1 በመቶ፣ ኢንዱስትሪ በ12.8 በመቶ፣ ማኑፋክቸሪንግ በ12.0 በመቶ፣ ኮንስትራክሽን በ12.3 በመቶ፣ አገልግሎት ደግሞ በ7.1 በመቶ የሚያድጉ መሆናቸው ተገምግሟል፡፡ ያለፉት 9 ወራት ጠቅላላ የመንግሥት ገቢ ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት አንጻር የ134 በመቶ ብልጫ አሳይቷል፡፡ የውጭ ብድር ከጠቅላላ የሀገር ውስጥ ምርት ያለው ድርሻ ወደ 13.7 በመቶ ወርዷል፡፡ ወደ ውጭ ገበያ የሚቀርቡት ስድስት ዋና ዋና ምርቶች፣ ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸሩ ከ82 በመቶ እስከ 386 በመቶ ጭማሪ አሳይተዋል፡፡ በስንዴ፣ በሩዝ፣ በቡና፣ በሻሂ ቅጠል እና በፍራፍሬ ምርቶች በአፍሪካ ቀዳሚ ሆኖ ለመውጣት እየተደረገ ያለው ትግል ፍሬ እያፈራ መሆኑን አይተናል፡፡ ውድ የብልፅግና አመራሮች፣ የብልፅግና አባላትና መላው ሕዝባችን፣ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ዝቅተኛ ኑሮ በሚኖሩ ወገኖች ላይ ጫና እንዳያሳድር አስፈላጊ የሆኑና የታቀዱ የድጋፍ መርሐ ግብሮች መከናወናቸውንም የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው መርምሯል፡፡ ለማዳበሪያ 62 ቢልዮን ብር፣ ለሴፍቲኔት 41.2 ቢልዮን ብር፣ ለነዳጅ 60 ቢልዮን ብር፣ ለመድኃኒት 3.5 ቢልዮን ብር፣ ለምግብ ዘይት 6.1 ቢልዮን ብር፣ እንዲሁም ለደመወዝ 38.4 ቢልዮን ብር ድጎማ ተደርጓል፡፡ ባለፉት 9 ወራት ብቻ 344790 የውጭ ሀገር ሕጋዊ የሥራ ዕድሎች እና ከ3 ሚልዮን በላይ የሀገር ውስጥ የሥራ ዕድሎች ተፈጥረዋል፡፡ የርቀት የሥራ ዕድሎች ቁጥርም እየጨመረ መምጣቱ ታይቷል፡፡ የመንግሥት የልማት ተቋማትን በአዲስ አስተሳሰብና በአዲስ መንገድ መልሶ ለማደራጀትና ለመምራት መቻሉ፣ እያስገኘው ያለው ውጤት ለሌሎች አርአያ የሚሆን እንደሆነ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ገምግሟል፡፡ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ሆልዲንግስ አሁን ያለው ጠቅላላ ገቢ 1.5 ትሪልዮን መድረሱ ታይቷል፡፡ ከባለፈው ዓመት የ9 ወራት አፈጻጸም አንጻር የዘንድሮ ገቢው የ86 በመቶ ጭማሬ ማሳየቱም ተረጋግጧል፡፡ ይሄም መንግሥት የሀገርን ሀብት ለማወቅ፣ ዐውቆም በሚገባ ለማስተዳደር፣ አስተዳድሮም ወረት ለማከማቸት የተከተለው መርሕ ትክክል መሆኑን አረጋግጧል፡፡ የውጭ ምንዛሬ ክምችት ዕድገት ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ 9 ወራት ጋር ሲነጻጸር የ203.99 በመቶ ዕድገት አሳይቷል፡፡ የባንኮች ተቀማጭ ገንዘብ ከ3 ትሪልየን በላይ ተሻግሯል፡፡ የ9 ወራት የወጪ ንግድ አፈጻጸም ከ5 ቢልዮን ዶላር በላይ ሲሆን፣ ይሄም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ150.39 በመቶ ዕድገት አምጥቷል፡፡ ባለፉት ስምንት ወራት 473.9 ቢልዮን ብር ብድር ከንግድ ባንኮች ተለቅቋል፡፡ ይሄም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ጊዜ አንጻር በ61.9 በመቶ ከፍ ይላል፡፡ ከዚህ ብድር ውስጥም 76.6 በመቶ ለግሉ ዘርፍ የተሰጠ ነው፡፡ ለግሉ ዘርፍ የበለጠ ብድር መሰጠቱ፣ የግሉ ዘርፍ በኢኮኖሚው ተገቢውን ሚና እንዲጫወት ያስቀመጥነው ፖሊሲ በተግባር እየተገለጠ መሆኑን አመላካች ነው፡፡ ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030ን ለማሳካት የጀመርናቸው ሁሉን አቀፍ ጥረቶች ፍሬያቸው እየጎመራ ነው፡፡ የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች 50.2 ሚልዮን፣ የሞባይል ተጠቃሚዎችም 86.6 ሚልዮን ደርሰዋል፡፡ የቴሌ ብር ደንበኞችም ከ52.56 ሚሊዮን በላይ ናቸው፡፡ ዲጂታል ፋይናንስ፣ የኅብረተሰቡን ፍትሐዊ ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ ባለፈ ለኢኮኖሚው መሣለጥ ጉልህ ድርሻ እያበረከተ ነው፡፡ ባለፉት 9 ወራት በዲጂታል መንገዶች 7.73 ቢልዮን ብር ተቆጥቧል፡፡ 26.77 ቢልዮን ብር በዲጂታል በኩል ብድር ተሰጠ ሲሆን፣ የ12.51 ትሪሊዮን ብር ግብይት ደግሞ በዚሁ መንገድ ተከናውኗል፡፡ ዋና ዋና ፕሮጀክቶችን በጊዜና በተገቢ ደረጃ ለማጠናቀቅ የተሰጠው አቅጣጫ ብዙዎችን ለፍጻሜ እያበቃቸው ነው፡፡ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ አፈጻጸም 98.66 በመቶ ደርሷል፡፡ የኮይሻ፣ አይሻና አሰላ የኃይል ማመንጫዎች በተያዘላቸው ዕቅድ መሠረት እየተጓዙ መሆናቸው ተገምግሟል፡፡ የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታም የኢትዮጵያን ነገ ታሳቢ ባደረገ መልኩ የቅድመ ዝግጅት ምእራፉ እየተከናወነ ይገኛል፡፡ የኮሪደር ልማት በአዲስ አበባ በ8 ኮሪደሮች እና በመላው ኢትዮጵያ በ65 ከተሞች እየተከናወነ መሆኑ ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ ብዙዎቹ የመስኖ ግድቦች ወደ ፍጻሜያቸው እየደረሱ ናቸው፡፡ ከዘጠኙ የመስኖ ግድቦች ውስጥ ስድስቱ አፈጻጸማቸው ከ75 በመቶ በላይ ደርሷል፡፡ “ትምህርት ለትውልድ” በሚል መሪ ቃል ከ82 ቢልዮን ብር በላይ ድጋፍ የተሰበሰበ ሲሆን፣ በአጠቃላይ 6815 ትምህርት ቤቶች በመላ ሀገሪቱ ተገንብተዋል፡፡ የነባር ትምህርት ቤቶችን ዐቅም ለማሻሻል እና በግጭት የተጎዱትን ለመጠገን የተደረገው ጥረት በትውልድ ላይ ለሚሠራው ሥራ መሠረት የሚጥል መሆኑ ታይቷል፡፡ የወላድ እናቶችን እና የጨቅላ ሕጻናትን ሞት በመቀነስ ረገድ የተሻለ ውጤት መመዝገቡም ታይቷል፡፡ በኢትዮጵያ የቱሪዝም መዳረሻዎችና የስፖርት ሥፍራዎች በቁጥርም፣ በዓይነትም እያደጉ መጥተዋል፡፡ በተለያዩ ከተሞች በመገንባት ላይ የሚገኙ ዓለም አቀፍ ስታዲየሞች በመጠናቀቂያ ምእራፍ ላይ ናቸው፡፡ ይሄም ኢትዮጵያ ታላላቅ አፍሪካዊ ጨዋታዎችን ለማስተናገድ ለያዘችው ዕቅድ መሳካት ወሳኝ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ፣ ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ኩነቶችን ለማስተናገድ ያላት መሠረተ ልማት እና የመስተንግዶ ዐቅም እያደገ ይገኛል፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከ66 በላይ ዓለም አቀፍ ኩነቶች በሀገራችን ተደርገዋል፡፡ በቱሪስት ፍሰት ጭማሪ ከአፍሪካ ቀዳሚ ሀገር በመሆን ላይ ነን፡፡ የኢትዮጵያን ተፈጥሯዊ፣ ባህላዊ፣ ታሪካዊ እና ሃይማኖታዊ ጸጋዎች አውጥተን ማሳየት ከቻልን፣ በቱሪዝም መስክ የቀዳሚነት ሚና መጫወት እንደምንችል ጅምሮቹ ያሳያሉ፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በተከናወኑ ተግባራት አምራችነትን በማበረታታት፣ ሥራ ያቆሙ ኢንዱስትሪዎችን ወደ ሥራ በማስገባት፣ ገቢ ምርቶችን በሀገር ውስጥ ምርት በመተካት፣ የሀገር ውስጥ ገቢን በማሰባሰብ፣ ወጪ ምርቶችን በብዛት በማምረት፣ ከአንድ ጊዜ በላይ መሬትን ደጋግሞ በማረስ፣ ሪፎርሞችን በየዘርፋቸው አግባብ በመተግበር፣ የተመዘገቡ ውጤቶች ተስፋ ሰጪ ናቸው፡፡ በዚህ እንቅስቃሴ የተነሣ ራስን የመቻል ተነሣሽነት ጨምሯል፡፡ ዘጠኝ ክልሎች ሰብአዊ ድጋፍን በራሳቸው ዐቅም ከመሸፈናቸውም በላይ የሰብአዊ ድጋፍ ፈላጊዎች ቁጥርም ባለፉት አምስት ዓመታት በሀገር አቀፍ ደረጃ በ86 በመቶ ቀንሷል፡፡ ሂደቱ ተረጂነትን መጸየፍና አምራችነትን ባህል ማድረግ በሀገራችን ሥር እየያዘ መሆኑን አመላካች ነው፡፡ ውድ የብልፅግና አመራሮች፣ የብልፅግና አባላትና መላው ሕዝባችን፣ እነዚህ ስኬቶች የጉዟችን መጀመሪያ እንጂ መጨረሻ አይደሉም፡፡ ማበረታቻዎች እንጂ ፍጻሜዎች አይደሉም፡፡ ስኬቶቹ መንገዳችን ትክክል መሆኑን የሚያሳዩ የተራራ ላይ መብራቶች ናቸው፡፡ ለበለጠ ሥራ የሚያነሣሡ፣ ለበለጠ ወኔ የሚቀሰቅሱ፣ የጠለቀ ቁጭት የሚቆሰቁሱ ናቸው፡፡ በሠራናቸው የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የጸጥታ ተቋማት ሪፎርሞች ሀገራችን ከነበረባት የህልውና አደጋ ወጥታ ወደ አስተማማኝ ህልውና እየተሻገረች ነው። ሪፎርሙ የነበረውን የህልውና ሥጋት መቀልበስ ብቻ ሳይሆን፣ የሀገርን ህልውና ለመጠበቅ የሚያስችል አስተማማኝ ዐቅም ፈጥሯል፡፡ ይሄም በተቃራኒው መንግሥትን በኃይል ለመጣል የነበረውን ፍላጎት አምክኗል፡፡ በተደረጉ ሀገር በቀል ማሻሻያዎች፣ በተፈጠረው ዐቅም እና ዝግጁነት ኢኮኖሚያችን ወደ ተሟላ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ ገብቷል፡፡ ይሄ ደግሞ የኢኮኖሚ ሂደታችንን እና የብልጽግና ጉዟችንን የሚቀይር አዲስ ምእራፍ ፈጥሯል። የሕዳሴ ግድብ መጠናቀቅ እና የባሕር በር ጉዳይ በቀጣናችን የአጀንዳ የበላይነት እንድንፈጥር አስችሎናል፡፡ በዚህም የተነሣ ሀገራችንን ከተከላካይነት ወደ ተጽዕኖ ፈጣሪነት አሸጋግሯታል። በመሆኑም ለውጡ ከመተከል ወደ ማንሠራራት ተራምዷል ማለት ይቻላል። መንግሥት የፈጠረው ዐቅም፣ የፀረ ለውጥ ኃይሉ መዳከም እና ዓለም አቀፍ ለውጡ የኢትዮጵያን ሪፎርም ለማሳካት የተሻለ ዕድል የሚሰጥ ነው፡፡ መንግሥትን በኃይል ለመጣልና ፍላጎትን በጉልበት ለማሳካት የሚደረገው መፍጨርጨር ውጤት እንደማያስገኝ ሀገራዊ እውነት እየሆነ ነው፡፡ በየጊዜው ወደ ሰላም የሚመጡት ታጣቂዎች ቁጥር መጨመርም ይሄንን ያመለክታል፡፡ በአንድ በኩል እነዚህን ስኬቶች ይበልጥ ማስፋትና ማጽናት አለብን፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ራሳችንን ከመሐል ዘመን ወጥመድ መጠበቅ ይገባናል፡፡ የመሐል ዘመን ወጥመድ፣ አንድ ሀገር ከፖለቲካ ሥርዓት ሽግግር በመውጣት፣ ወደ ቀጣዩ የማጽናት ምእራፍ ከመድረሷ በፊት፣ በሚገኘው የመሐል ዘመን፣ በስኬቶች ረክቶና ተዘናግቶ የመቀመጥ አባዜ ነው፡፡ ከፖለቲካ ሽግግር በመውጣትና የጸና ሥርዓትን በመትከል መካከል የሚገኝ ፈታኝ ዘመን ነው፡፡ የሀገራችን ኢኮኖሚ በማደግ ላይ ያለ እንጂ በሚፈለገው መጠን ያደገ አይደለም፡፡ በግብርና፣ በኢንዱስትሪ፣ በከተማ ልማት፣ በወጪ ምርቶች፣ በማዕድን፣ በአገልግሎት ዘርፍ፣ በዲጂታል ኢትዮጵያ፣ ወዘተ. ያየናቸው ለውጦች ብንሠራ የት እንደምንደርስ አመላካቾች ናቸው፡፡ ከግባችን መድረሳችንን ግን አያበሥሩም፡፡ የፖለቲካ ባህላችን እየተለወጠ ነው፤ ነገር ግን የሠለጠነ የፖለቲካ ባህል ገና አልገነባንም፡፡ የጸጥታ ተቋሞቻችን እየዘመኑና እየደረጁ ናቸው፤ ይሁን እንጂ በኢትዮጵያ ልክ ገና አልደረሱም፡፡ የፖለቲካ ፍላጎትን በኃይል የማስፈጸም አካሄድ ፋሽኑ እያለፈበት መጥቷል፡፡ ነገር ግን ገና ከፖለቲካና ከማኅበራዊ ባህላችን ተፍቆ አልጠፋም፡፡ የሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም ገና በጅምር ላይ ነው፡፡ ዕዳችን ቢቃለልም ገና ከጫንቃችን ፈጽሞ አልወረደም፡፡ የዋጋ ግሽበትን ብንቋቋመውም፣ የኑሮ ውድነትን ግን በተገቢው መንገድ ገና አላቃለልነውም፡፡ በመሆኑም ከስኬት ማማ ላይ የደረስን መስሎን፣ በመሐል ዘመን ወጥመድ እንዳንያዝ አመራሮችና አባላት ነቅተው እንዲታገሉ፣ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴው በአጽንዖት ያሳስባል፡፡ የመሐል ዘመን ወጥመድ በዋናነት የሚከሠተው በውጤት በመዘናጋት፣ ችግርን በመላመድ፣ ሀገራዊ ዕይታን ትቶ በጎጥ ውስጥ በማደር እና የሕዝብን ችግሮች በጊዜያቸውና በልካቸው ባለመፍታት ነው፡፡ በመሆኑም እነዚህ ችግሮች የመሐል ዘመን ወጥመድን እንዳያመጡብን በአመራሩና በአባላቱ ዘንድ ትግል ሊደረግባቸው ይገባል ፡፡ ውድ የብልፅግና አመራሮች፣ የብልፅግና አባላትና መላው ሕዝባችን፣ የተዛባ ትርክት እንዳይፈጠር የብሔራዊ ዐርበኝነት ትርክትን በሚገባ ማሥረጽ ይጠበቅብናል፡፡ የሕዝብን ጥያቄዎች በየደረጃው መፍታት አለብን፡፡ ምርትና ምርታማነትን ከፍ በማድረግ የኑሮ ውድነትን የሚያቃልሉ ሥራዎችን መሥራት ይጠበቅብናል፡፡ የተጀመሩ ኢኒሼቲቮችን የሕዝብ ርካታ በሚፈጥሩ መልኩ ወደ ውጤት ማድረስ አለብን፡፡ ከጠላቶቻችንን ላይ የመሣሪያም የትርክትም ትጥቅ ማስፈታት ይገባል፡፡ ለጠላት ተጋላጭነትን ሊፈጥሩ የሚችሉ አሠራሮችን ማረም ጊዜ የማይሰጠው ተግባር ነው፡፡ የአመራር ሥምሪትን መፈተሽና ማጥራት መንገዳችንን የበለጠ ምቹ ያደርገዋል፡፡ ትጋትና ቁርጠኝነትን መጨመር፣ መናበብንና ቅንጅትን ማሣለጥ አለብን፡፡ ኅብረ ብሔራዊ አንድነትን የሚፈጥሩ፣ ገዥ ትርክትን የሚያሠርጹ፣ ብሔራዊ ጥቅሞቻችንን የሚያስከብሩ እና የኢትዮጵያን ብልጽግና የሚያረጋግጡ ተግባራትን ባለማሰለስ በየአካባቢያችን ተግተን ማከናወን ያስፈልገናል፡፡ የክረምት የበጎ ፈቃድ ሥራዎችን በተገቢ ዕቅድ እና ቅንጅት መርተን ለውጤት ማብቃት ይገባናል፡፡ በአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ ግብር በዚህ ዓመት የተያዘውን ዕቅድ ለማሳካት ሕዝቡን የማትጋትና የማሳተፍ ሥራ ከአሁኑ መጀመር አለበት፡፡ ለመኸር የእርሻ ሥራዎች የሚያስፈልጉ ግብዓቶችና ማሽነሪዎች በተገቢ ቦታና ጊዜ እንዲደርሱ የአመራር ሚናችንን እንወጣ፡፡ አንድም መሬት ጦም በማያድርበት ሁኔታ የግብርና ሥራዎች እንዲከናወኑ እናድርግ፡፡ በአጠቃላይ፣ በሰላማዊ እና በሠለጠነ መንገድ ልዩነቶቻችን በመፍታት፣ የጀመርናቸው ሪፎርሞች በማሳካት፣ የገጠሙንን ፈተናዎች በጽናት በማለፍ፣ ተግዳሮቶቻችንን በመጋፈጥና በማሸነፍ፣ የኢትዮጵያን ብልጽግና እውን እንድናደርግ፣ የብልፅግና ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ለብልፅግና ፓርቲ አመራርና አባላት፣ ለተፎካካሪ ፓርቲዎች እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጥሪ ያቀርባል፡፡ የብልፅግና ፓርቲ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ሚያዝያ 18/ 2017፤ አዲስ አበባ