ፖለቲካ
የባህርዳር ከተማ የልማት ስራዎች የአመራሩ የትጋት ውጤት ማሳያዎች ናቸው
Dec 3, 2023 41
ባህር ዳር፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ)፡- የመንግስት አመራሮች በፈተናዎች ሳይረበሹ ለህዝብ ተጠቃሚነት መስራት እንዳለባቸው በባህርዳር ከተማ እየተገነቡ ያሉ መሰረተ ልማቶች ማሳያ ናቸው ሲሉ የአራተኛ ዙር ሰልጣኝ የአመራር አባላት ገለጹ። በባህር ዳር ከተማ እየተሰጠ ያለውን ሥልጠና የሚከታተሉ የመንግስት አመራር አባላት በከተማው እየተገነቡ የሚገኙ የመሰረተ ልማቶችን ጎብኝተዋል። ከሰልጣኞቹ መካከል አቶ ደመላሽ በላይ እንደገለጹት፤ በክልሉ ካለው ወቅታዊ የጸጥታ ችግርና ማህበራዊ ሚዲያው እያጋነነ ከሚያናፍሰው መረጃ አኳያ ወደ ባህር ዳር መምጣት ጉዳይ አሳስቧቸው ነበር። ይሁን እንጂ በከተማዋ ተገኝተው በተግባር የተመለከቱት እንደሚለይ አስታውሰው፤ ሰላማዊ፣ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በአግባቡ እየተከናወኑ መሆናቸውን መታዘብ እንደቻሉ ገልጸዋል። የከተማዋ አመራር ተቀናጅቶ እያከናወናቸው ያሉ ሥራዎች በችግር ውስጥም ሆኖ መስራት እንደሚቻል ያሳዩና በአርአያነት የሚጠቀሱ መሆናቸውን እንደተረዱ ተናግረዋል። “በባህር ዳር ከተማ እየተገነቡ ያሉ መሰረተ ልማቶች ማህበረሰቡ ከመንግስትና ከልማት ስራዎች ያልተነጠለ መሆኑን ማሳያዎች ናቸው“ ያሉት ደግሞ አቶ መሀመድ ካሣ ናቸው። ''በባህር ዳር ከተማ ቆይታችን የመንግስት አመራር አባልና የጸጥታ አካላት ሃላፊነታቸውን በአግባቡ እየተወጡ መሆናቸውን እየተገነቡ ያሉት የልማት ስራዎች ምስክሮች ናቸው'' ብለዋል። ወይዘሮ በየነች ቲንኮ በበኩላቸው፤ የባህር ዳር ከተማ አመራር አካላት ጥረት ወቅታዊ ችግሮችን በመቋቋም በየዘርፉ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች በፈተናዎች ውስጥም ሆኖ እቅዶችን ማሳካት እንደሚቻል የሚያስመሰክር እንደሆነ ተናግረዋል። የባህር ዳር ከተማ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በማህበራዊ የትስስር ገጾች ስለ ባህር ዳር ከሚናፈሰው የሃሰት ፕሮፖጋንዳ ስራዎች በተግባር በአርዓያነት የሚጠቀሱ የልማት ተግባራትን ማደብዘዝ እንዳልቻሉም ገልጸዋል። የባህር ዳር ከተማ አስተዳደር ከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ ወንዳለ ጋሻው እንዳሉት፤ የአመራር አባላት ጉብኝት ከተማዋን የበለጠ ለቱሪዝምና ለኢንቨስትመንት ምቹ ለማድረግ ያግዛል። የከተማ አስተዳደሩ የስፖርት ማዘውተርያ አገልግሎትን ጨምሮ ሁሉን አቀፍ አገልግሎት የሚሰጡ የአረንጓዴና ሌሎች በርካታ የልማት ስራዎች እያከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ''ከዕዳ ወደ ምንዳ'' በሚል መሪ ሃሳብ እየተሳተፉ የሚገኙት ሰልጣኝ አመራር አባላት በከተማዋ እየተከናወኑ የሚገኙ የአረንጓዴና ሌሎች የመሰረተ ልማት ስራዎችን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።
የጋራ እሴቶቻችንን በማጎልበት የህዝብ ለህዝብ ትስስሩን ለማጠናከር  እንሰራለን - ሰልጣኝ አመራር አባላት
Dec 3, 2023 48
ጅንካ፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ) ፦ የጋራ እሴቶቻችንን በማጎልበት የህዝብ ለህዝብ ትስስሩን ለማጠናከር የሚጠበቅባቸውን ለመወጣት መዘጋጀታቸውን ሰልጣኝ የመንግስት አመራር አባላት ገለጹ ። 4ኛው ዙር የመንግስት አመራር አባላት የአቅም ግንባታ ስልጠና በጂንካ ማዕከል እየተሰጠ ሲሆን ከተለያዩ የሀገሪቱ አከባቢዎች የተወጣጡ ከ700 በላይ አመራሮች ስልጠናውን እየተከታተሉ ነው። ኢዜአ ያነጋገራቸው አመራር አባላቱ ልዩነቶችን በማጥበብ፣ የጋራ እሴቶቻችንን በማጎልበት የህዝብ ለህዝብ ቅርርቡን ለማጠናከር የሚጠበቅባቸውን ለመወጣት አበክረው እንደሚሰሩም ተናግረዋል። ከኦሮሚያ ክልል ከቦረና ዞን የተሳተፉት አቶ ዋሪዮ ቦሩ እንደገለፁት፤ የአቅም ግንባታ ስልጠናው አመራሩ በአገራዊ ጉዳይ ላይ ተቀራራቢ እይታ እንዲኖረው አስችሏል። አገራችንን ከ"ዕዳ ወደ ምንዳ" ለማሸጋገር የተወጠነውን አገራዊ ራዕይ እድገትና፣ ብልፅግናን ዕውን ለማድረግ የአመራሩ የተግባርና የአስተሳሰብ አንድነት እንደሚያስፈልግ አንስተዋል። በዚህም በአመራሩ ዘንድ የተግባርና የአስተሳሰብ አንድነት መፍጠር ከተቻለ አገራዊ ሰላም እና አንድነት በጋራ ጥረት ማምጣት እንደሚቻል ተናግረዋል ። ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከጌዴኦ ዞን የመጡት ወይዘሮ አለምፀሐይ ሽፈራው በበኩላቸው የአቅም ግንባታ ስልጠናው ሁለንተናዊ ዕውቀት ያገኘንበት ነው ብለዋል። ስልጠናው በአመራሩ ዘንድ ወጥ የሆነ አገራዊ አመለካከት እንዲኖር ከፈጠረው ምቹ አጋጣሚ በተጨማሪ አመራሩ ለጋራ ችግሮች የጋራ መፍትሔ ማመንጨት የሚችልበትን አቅም ፈጥሯል። ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከስልጤ ዞን የተሳተፉት አቶ ሀያቱ ሙክታር ፥ "የአቅም ግንባታ ስልጠናው ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባትና በሀገሪቱ ዘላቂ ሰላም ለማምጣት የሚያስችል እውቀት እና ክህሎት ያገኘንበት" ነው ብለዋል። ሀገራችን ብዙ ፀጋዎች አሏት ያሉት አቶ ሀያቱ፤ይህንን ፀጋ በማልማት በአጭር ጊዜ ከድህነት ለመውጣት አመራሩ ከፋፋይ አስተሳሰቦችን ማስወገድ እና ህዝብ ለህዝብ የሚያቀራርቡ እሴቶችን በማጉላት ህዝቡን ለልማት ማነሳሳት እንዳለበት አንስተዋል። ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከኮንሶ ዞን የመጡት አቶ ታደለ ሮባ፥ ለመፍጠር የታሰበውን ሀገራዊ መግባባትና ዘላቂ ሰላም ዕውን ለማድረግ የፊት አመራሩ የሚጠበቅበትን ሊወጣ ይገባል ነው ያሉት። ሀገራዊ ሰላም፣ ልማትና ብልፅግናን ለማረጋገጥ የተዛቡ ትርክቶችን ማቃናትና የህዝብ ለህዝብ ቅርርቡን ማጠናከር እንዲሁም ወንድማማችነትን በማጉላት ረገድ ሁሉም የበኩሉን ጥረት ማድረግ እንዳለበትም አንስተዋል ። አመራሩ በሀገሪቱ ዘላቂ ሰላምና ልማትን ለማምጣት በሀገሪቱ በሚገኙ ቱባ ባህሎች ውስጥ ያሉ ሀገር በቀል ዕውቀቶችን ማጉላት እንዳለበት ያነሱት ደግሞ ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከጋሞ ዞን የመጡት የስልጠናው ተሳታፊ አቶ ተስፋዬ አላዛር ናቸው። በዚህ ረገድ በቱባ ባህሎች ውስጥ ያሉ ስለ ሰላም፣ ስለ አንድነትና ስለ አብሮነት የሚያስተምሩ ባህላዊ እሴቶችን ለትውልዱ በማስተማር ረገድ አመራሩ ሚናውን ሊወጣ ይገባል ካሉ በኋላ ''እኔምየድርሻዬን ለመወጣት እተጋለሁ'' ብለዋል ። ''አንድነት አቅም ነው፣ አንድነት ልማት ነው ፣ አንድነት አብሮ ማደግ ነው'' ያሉት አስተያየት ሰጪው፤ ለአንድነታችን፣ ለአብሮነታችን እና ለሰላማችን ቅድሚያ በመስጠት እንሰራለን ሲሉም አክለዋል።  
ለሀገራዊ አንድነት ብዝሃነትን ጠንካራ መሰረት በማድረግ የበለጸገችና ለሁላችንም የምትመች ሀገር መገንባት አለብን-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Dec 3, 2023 57
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ)፦ ለሀገራዊ አንድነት ብዝሃነትን ጠንካራ መሰረት በማድረግ የበለጸገችና ለሁላችንም የምትመች ሀገር በጋራ መገንባት አለብን ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ተናገሩ። 18ኛው የብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ቀን "ብዝሃነትና እኩልነት ለአገራዊ አንድነት" በሚል መሪ ሃሳብ በተለያዩ ዝግጅቶች በመከበር ላይ ይገኛል።   እለቱን በማስመልከትም በአዲስ አበባ ወዳጅነት አደባባይ የባህል ፌስቲቫል ተካሒዷል፡፡ በመድረኩ ላይ መልእክት ያስተላለፉት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ የብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ሕዝቦች ቀን የሚከበረው በብዝሃነት አገራዊ አንድነትን ለማጠናከር መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም ለሀገራዊ አንድነት ብዝሃነትን ጠንካራ መሰረት በማድረግ የበለጸገችና ለሁላችንም የምትመች ሀገር በጋራ መገንባት አለብን ብለዋል። በኢትዮጵያ ለልዩነት ምክንያት የሆኑ ነጠላ ትርክቶችን በመተው አንድነትን የሚያጠናክሩት ላይ ማተኮር አለብን ብለዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ቡዜና አልከድር፤ የዕለቱ መከበር ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ህዝቦች የባህል ትስስር በመፍጠር ሀገራዊ አንድነትን ለማጠናከር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። የብሔር ብሔረሰቦች በዓል በዚህ መልኩ መከበሩ እርስ በእርስ ለመተዋወቅ፣ ለባህል ትስስርና ለጋራ የሀገር ግንባታ ወሳኝ መሆኑን የፌስቲቫሉ ተሳታፊዎች ተናግረዋል። 18ኛው የብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ቀን በሀገር አቀፍ ደረጃ ህዳር 29 ቀን 2016 ዓ.ም በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ከተማ የሚከበር ይሆናል።
የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ለማረጋገጥ ጠንካራ የፖሊስ ተቋም የመገንባት ስራ በተጠናከረ መልኩ ይቀጥላል- ም/ኮሚሽነር ጀነራል መላኩ ፈንታ
Dec 3, 2023 51
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ)፡- የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ለማረጋገጥ ጠንካራ የፖሊስ ተቋም የመገንባትና የሰው ሃይል የመፍጠር ስራ በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል መከላከል ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል መላኩ ፈንታ ገለጹ። ለአዲስ አበባ ፖሊስ ከፍተኛ አመራሮች ከህዳር 17 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ በአፍሪካ የአመራር ልህቀት አካዳሚ ለአንድ ሳምንት ሲሰጥ የነበረው ስልጠና ተጠናቋል።   የስልጠናው ትኩረትም ተቋማዊ ሪፎርም፣ የፖሊስ ስነ-ምግባርና የለውጥ አመራር፣የተቋም ግንባታና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን ያካተተ ነው። በስልጠናው ማጠቃለያ ላይ የተገኙት የፌዴራል ፖሊስ ወንጀል መከላከል ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል መላኩ ፈንታ፤ የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ማረጋገጥ የሚቻለው ጠንካራ የፖሊስ ተቋምና አመራር መፍጠር ሲቻል መሆኑን ተናግረዋል። የአዲስ አበባ ፖሊስ አመራርና አባላት የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ለማስጠበቅ እያደረጉት ላለው የላቀ ሚና አመስግነው በቀጣይም ለተሻለ አፈፃፀም እንዲዘጋጁ አሳስበዋል። ለዚህም የፖሊስን አቅም በሁሉም መልኩ ማጎልበትና ለወንጀል መከላከል እና የምርመራ ስራ የሚያግዙ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን በስፋት መጠቀም ይገባል ብለዋል። በመሆኑም የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ለማረጋገጥ ጠንካራ የፖሊስ ተቋም የመገንባትና የሰው ሃይል የመፍጠር ስራ በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው በበኩላቸው ስልጠናው የተቋሙን ተልዕኮ መነሻ በማድረግ የተካሄደ መሆኑን ጠቅሰው በቀጣይነት እስከ አባሉ የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል።   የስልጠናው ተሳታፊ አመራሮችም በቀጣይ ለተሻለ ስራ የሚያዘጋጅ ስልጠና ማግኘታቸውን ገልጸው ለተሻለ ስራ መዘጋጀታቸውን አረጋግጠዋል።
ጅቡቲ ከኢትዮጵያ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በቂ ትምህርት ወስዳለች - መሀመድ አብዱላኢ ሙሳ
Dec 3, 2023 51
አዲስ አበባ፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ)፦በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብር በኢትዮጵያ ከተከናወነው ተግባር ጅቡቲ በቂ ትምህርት ወስዳበታለች ሲሉ የሃገሪቱ የአካባቢ ጥበቃና የዘላቂ ልማት ሚኒስትር መሀመድ አብዱላኢ ሙሳ ገለጹ። ኢትዮጵያ በተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ዱባይ እየተካሄደ ባለው ኮፕ 28 የአየር ንብረት ጉባኤ ላይ ያዘጋጀችውን አረንጓዴ አሻራ መካነ ርዕይ/ፓቪሊዮን የሃገራት መሪዎች፣የጉባኤው ተሳታፊዎች እየጎበኙት ነው። ፓቪሊዮኑን የጎበኙት ሚኒስትር መሀመድ አብዱላኢ ሙሳ እንደተናገሩት በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ አነሳሽነት ኢትየጵያ ባለፉት አምስት አመታት በአረንጎዴ ልማት ያከናወነቻቸው ተግባራት ትልቅና የሚያስደንቁ ናቸው። በቀጣይም ጅቡቲ በኢትዮጵያ የተከናወነውን የአረንጎዴ ልማት ተግባራዊ ለማድረግ በአገሪቱ ግብርና ሚኒስቴር በኩል የተጠናከሩ ስራዎችን በትኩረት እንደምትሰራ ተናግረዋል። ኢትዮጵያና ጅቡቲ የረጅም ጊዜ ግንኙነት ያላቸው ወዳጅ አገሮች መሆናቸውን ያነሱት ሚኒስትሩ በትራንስፖርትና በኤሌክትሪክ ዘርፍ ብቻ ሳይሆን በአካባቢ ጥበቃ ላይም በጋራ እየሰሩ መሆናቸውን አንስተዋል። ኢትዮጵያ በአረንጎዴ ልማት ስራ ለጅቡቲ በርካታ ችግኞችን በመለገስ የአረንጎዴ አሻራ እንዲስፋፋ ያደረገችው አሰተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑንም ገልጸዋል።
በሕብረ ብሔራዊ ወንድማማችነትና እህትማማችነት ባጌጠችው  አዲስ አበባ 18ኛውን የብሄር ብሄረሰቦች ቀን አክብረናል - ከንቲባ አዳነች አቤቤ 
Dec 3, 2023 70
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያውያን በሕብረ ብሔራዊ ወንድማማችነትና እህትማማችነት ባስጌጧት የሁላችን ቤት በሆነችው አዲስ አበባ 18ኛውን የብሄር ብሄረሰቦች ቀን አክብረናል ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ 18ኛው የብሔር ብሔረሰቦች ቀን ማጠቃለያ የባህል ፌስቲቫል በከተማችን ተከናውኗል ሲሉም በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ገልጸዋል።   አክለውም ኢትዮጵያውያን በሕብረ ብሔራዊ ወንድማማችነትና እህትማማችነት ባስጌጧት የሁላችን ቤት በሆነችው አዲስ አበባ “ብዝሃነትና እኩልነት ለሃገራዊ አንድነት” በሚል መሪ ቃል 18ኛውን የብሄር ብሄረሰቦች ቀን ዛሬ ረፋድ ላይ አክብረናል ብለዋል።   ብዝሀነት ነባራዊ ሀቅ፣ መዋቢያችን፣ መድመቂያችን መሆኑን ተገንዝበን ከሃገራዊ አንድነታችን ጋር አስተሳስረን በትጉሀን እጆች ወደ ብልፅግና እየገሰገሰች ያለችውን ኢትዮጵያን በሁላችን ትጋት ራዕይዋን እውን ማድረግ እንቀጥላለን ሲሉም ከንቲባ አዳነች ገልጸዋል።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የጸረ ሙስና ትግልን ስኬታማ ለማድረግ የሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል 
Dec 3, 2023 65
ሆሳዕና፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ)፦የጸረ ሙስና ትግሉ ስኬታማ እንዲሆን በየደረጃው የሚገኙ የመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ማህበረሰቡ ጠንካራ ተሳትፎ ማድረግ እንዳለባቸው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው አሳሰቡ ። "ሙስና የጋራ ጠላታችን ነው! በጋራ እንታገለው!! " በሚል መሪ ሃሳብ የጸረ ሙስና ቀን በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል። በመድረኩ ላይ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ እንዳሻው ጣሰው በክልሉ ብልሹ አሰራርና የሙስና ድርጊቶችን ለመቀነስ ብርቱ ትግል እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም የመንግስት አገልግሎትን በዝምድና፣ በሙስናና በመሰል ተደግፎ የሚሰጥ ከሆነ ብልሹ አሰራርን እያስፋፋ መንግስትንም ሆነ ህዝብን ለከፋ አደጋ ይዳርጋል ብለዋል ። ሙስናና ብልሹ አሰራር ዕድገትን እያቀጨጨ ለልዩነቶች ምንጭ በመሆኑ ችግሩን ለመከላከል በሚደረገው ጥረት በየደረጃው ያለው የመንግስት አመራርና ማህበረሰቡ ሃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል ብለዋል። የሀይማኖትና የትምህርት ተቋማት በስነ ምግባር የታነፁ ዜጎችን ለማፍራት የሚደረገውን ጥረት በማሳካት ረገድም የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡም ጠይቀዋል ።   የክልሉ ስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ማሞ ቴጌ በበኩላቸው ሙስናና ብልሹ አሰራር በዜጎች ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ለመከላከል ግንዛቤን የማሳደግ ስራ የኮሚሽኑ ትኩረት መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም ማህበረሰቡ ጥረቶችን በመደገፍ የሚጠበቅባቸውን እንዲወጡም ጠይቀው በተለይም አገልግሎቶችን በእጅ መንሻ ለመፈጸምም ሆነ ለማስፈጸም ከሚደረግ ጥረት በመቆጠብ የትግሉ አካል ሊሆኑ እንደሚገባ ተናግረዋል። በክልሉ ባለፉት 100 ቀናት ውስጥ በተለያዩ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ኮሚሽኑ ጥናትና ክትትል በማድረግ ተጋላጭ መስሪያ ቤቶች መለየቱን ጠቁመው በቀጣይም በህግ የሚጠየቁበት ስርዓት ለማበጀት ስራ መጀመሩንም ገልጸዋል።   ከተሳታፊዎች መካከል በክልሉ ጤና ቢሮ የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወይዘሮ ኤልሳቤጥ በጋሻው ሙስናና ብልሹ አሰራር ለዕድገት ጸር የሆነ አለፍ ሲልም ለሰላም እጦት ምክንያት ሊሆን እንደሚችል ገልጸዋል ። ህገ ወጥ የመድኃኒት ዝውውሮችና ሌሎች ጎጂ ተግባራት በቢሮ ደረጃ መኖራቸውን አንስተው በተቀናጀ መንገድ ለመከላከል ጥረቶች እየተደረጉ እንደሆነም አንስተዋል። በዞኑ የሚስተዋሉ የሙስናና የብልሹ አሰራሮችን ከጅምሩ ለመግታት ጥረቶች መኖራቸውን የተናገሩት በጉራጌ ዞን አስተዳደር የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና የስራ ሂደት አስተባባሪ አቶ ጀማል አህመድ ናቸው። በባለፉት ሶስት ወራት በተሰራ ስራ ከ340 ሄክታር በላይ በከተማና በገጠር በህገ ወጥ መንገድ የተወረሩ የመሬት ይዞታዎችን ጨምሮ በተለያየ መንገድ የተመዘበረ የህዝብና የመንግስት ሀብት ማስመለስ መቻሉን አብራርተዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋጤ ሱርሞሎ፣ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ኤርሲኖ አቡሬን ጨምሮ ሌሎች የክልሉና የዞን ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል።  
በአማራ ክልል ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ከመፍጠር በተጓዳኝ የልማት ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ ነው-  ዶክተር አህመዲን ሙሀመድ
Dec 3, 2023 51
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 23/2016 (ኢዜአ) ፦ በአማራ ክልል ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ከመፍጠር በተጓዳኝ የልማት ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑ ተገለጸ። የአማራ ክልል ከተሞች ልማት ዘርፍ አስተባባሪና የከተማና መሠረተ ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አህመዲን ሙሀመድ፤ የክልሉን ወቅታዊ ሁኔታ በሚመለከት ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በማብራሪያቸውም በክልሉ በተለያዩ አካባቢዎች በተደረጉ የውይይት መድረኮች የልማትና የመልካም አስተዳደር፣ የሰላም ጉዳይ፣ የኑሮ ውድነትና ስራ አጥነት በህዝቡ በተደጋጋሚ የተነሱ ጥያቄዎች መሆናቸውን አንስተዋል። በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ጠቅላይ መምሪያ እዝ ስር የሚመራው ኮማንድ ፖስትም በክልሉ አዲስ የተደራጀውን አመራር በማገዝ ሰላምና መረጋጋት እንዲፈጠር እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም በክልሉ ከላይ ጀምሮ እስከ ቀበሌ የተዋቀረው አመራር በተቀናጀ መልኩ የህዝቡን ጥያቄዎች ለመመለስ ሌት ከቀን እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በተለይም ዘላቂ ሰላም የመፍጠርና ልማትን የማስቀጠል እንዲሁም በየሴክተሩ የህዝብን ጥያቄዎች በሂደት የመመለስ ስራ እየተከናወነ መሆኑን አብራርተዋል። አዲስ የተደራጀው የክልሉ የፖለቲካና የጸጥታ አመራር በአገር አቀፍ ደረጃ በተዘጋጁ ሥልጠናዎች ላይ በመሳተፍ ህዝብን ለማገልገል የሚያስችል ተነሳሽነትን ልምድ ማግኘቱንም አንስተዋል። በመድረኮቹ በመልካም አስተዳደር፣ በልማት፣ በኑሮ ውድነት፣ በሰላምና ደህንነትና ሌሎችም ከህዝብ የተነሱ ጥያቄዎችን በቅጡ በመረዳት ወደ ተግባራዊ ምላሽ መገባቱንም ተናግረዋል። በመሆኑም በክልሉ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ከመፍጠር በተጓዳኝ የልማት ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። በየደረጃው የተመደቡ የስራ ኃላፊዎች የተጀመሩ በጎ ስራዎችን በማስቀጠል ህዝብ በጉድለት የሚያነሳቸውን ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት በቁርጠኝነት ሌት ተቀን እየሰሩ መሆኑንም ዶክተር አህመዲን አረጋግጠዋል። የክልሉን ዘላቂ ሰላም በማጽናት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመረውን ጥረት በማገዝ ህዝቡ እገዛና ትብብሩን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።
በአፋር ክልል ለሀገራዊ ምክክር አጀንዳ የሚያሰባስቡ ተሳታፊዎች መረጣ መጀመሩን ኮሚሽኑ አስታወቀ
Dec 2, 2023 62
ሰመራ፤ ህዳር 22/2016 (ኢዜአ)፦ በአፋር ክልል ለሀገራዊ ምክክር አጀንዳ የሚያሰባስቡ ተሳታፊዎች መረጣ ዛሬ በሰመራ ሎጊያ ከተማ መጀመሩን የኢትየጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አስታወቀ። ዛሬ በሰመራ ሎጊያ ከተማ አስተዳደር በተካሄደ ለሀገራዊ ምክክር አጀንዳ የሚያሰባስቡ ተሳታፊዎች መረጣም 36 ተወካዮች መለየታቸውን ኮሚሽኑ ገልጿል። በመረጣው ሂደት ከዘጠኝ የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች የተውጣጡ 180 ተሳታፊዎች የተገኙ ሲሆን 36 የህብረተሰብ ተወካዮችም ተመርጠዋል።   የተመረጡት የህብረተሰብ ተወካዮች የጎሳ መሪዎች፣ የሐገር ሽማግሌዎች፣ አርብቶ አደሮች፣ ሴቶች፣ ወጣቶች፣ የመንግስት ሠራተኞች፣ መምህራን፣ የንግድ ማህበረሰቡና ተፈናቃዮች ማካተታቸው ተገልጿል። በሰመራ ሎጊያ ከተማ ዛሬ ተሳታፊዎችን ለመምረጥ በተዘጋጀው መድረክ ላይ የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሸነር ዶክተር አይሮሪት መሐመድ እንዳሉት፣ መሠረታዊ በሆኑ አገራዊ ጉዳዮች ላይ የሀሳብ ልዩነቶችና አለመግባባቶች ሲንጸባረቁ ይታያሉ። ይህንን ልዩነትና አለመግባባት ዘላቂ በሆነ መንገድ ለመፍታት አገራዊ የህዝብ ምክክሮችን ሁሉን ባሳተፈ አግባብ ለማካሄድ መንግስት ትኩረት ሰጥቶ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። ይሄም አገራዊ መግባባትን በቀጣይ ለመፍጠር እንደሚያስችል ያመለከቱት ዶክተር አይሮሪት፣ በኮሚሽኑ የሚዘጋጁ የህዝብ ምክክሮች አገራዊ መግባባትን ለመፍጠር ያለሙ መሆናቸውን ገልጸዋል። በሂደትም በህዝቦች መካከል መተማመንና አብሮነትን በማጠንከር እየተሸረሸሩ ያሉ እሴቶችን ለማደስ የሚያግዙ መሆኑን ተናግረዋል። ኮሚሽኑ ዛሬ በሰመራ ሎጊያ ከተማ ለሀገራዊ ምክክር አጀንዳ የሚያሰባስቡ ተሳታፊዎች መረጣ ማካሄዱን ገልጸው፣ የተሳታፊዎች መረጣ በቀጣይም በሌሎች የክልሉ አካባቢዎች እንደሚካሄድ ጠቁመዋል። በእዚህ ታሪካዊ ሂደት የክልሉ ህዝብ ንቁ ተሳታፊ በመሆን ለአገራዊ ምክክሩ መሳካት የበኩሉን እንዲወጣም ኮሚሽነሯ ጥሪ አቅርበዋል። እንደ ኮሚሽነሯ ገለጻ ለሀገራዊ ምክክር አጀንዳ የሚያሰባስቡ ተሳታፊዎች መረጣ ላይ በክልሉ የተለያዮ የማህበረሰብ ክፍሎችን የወከሉ ተሳታፊዎች እንዲሳተፉ ይደረጋል። የአጀንዳ አሰባሳቢ ተወካዮች መረጣው አካታችነትን፣ ግልጽነትን፣ አሳታፊነትንና ተዓማኒነትን ያገናዘበ እንዲሆን ኮሚሽኑ የበኩሉን ድጋፍ እያደረገ መሆኑንም አስረድተዋል። በዛሬው ዕለት በተካሄደው የተወካዮች መረጣ ሰመራ ከተማን ወክለው ከአርብቶ አደር የማህበረሰብ ክፍል የተመረጡት አቶ ኖራ ኢሴ በበኩላቸው እስከገጠር ቀበሌ ድረስ በመሄድ ለሀገራዊ ምክክሩ መሳካት የበኩላቸውን እንደሚወጡ ገልጸዋል። በሎጊያ ከተማ ወጣቶችን በመወከል የተመረጠው ወጣት መሐመድ ቃሲም በበኩሉ በህብረተሰቡ በተለይም በወጣቱ የሚነሱ ጥያቄዎችን ለይቶ ለማውጣት ጠንክሮ እንደሚሰራ ገልጿል። በተለይ ሀገራዊ ፋይዳና ለህዝቦች አብሮነት ጠቀሜታ ያላቸውን ጉዳዮች በአጀንዳነት እንዲያነሱ የማድረግ ሃላፊነቱን በአግባቡ ለመወጣት ዝግጁነቱን አረጋግጧል። ሌላው የተወከለው መምህር ዘሪሁን ታዲዮስ በበኩሉ፣ አገራዊ ምክክሩ ለሰላምና ለሁለንተናዊ እድገት ያለውን ጠቀሜታ በማስረዳት አጀንዳ የማሰባሰብ ሥራውን በታማኝነት እንደሚወጣ ተናግሯል። በአፋር ክልል በ48 ወረዳዎችና ከተማ አስተዳደሮች የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች የሚወክሉ 864 ተሳታፊዎች እንደሚመረጡ ለማወቅ ተችሏል።  
ብዝሃነትን እንደ ፀጋ በመቀበል ለሰላም፣ ለልማትና ዴሞክራሲ መስራት ይጠበቅብናል - ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ
Dec 2, 2023 81
ሀዋሳ ፤ ህዳር 22/2016 (ኢዜአ)፡- ብዝሃነትን እንደ ፀጋ በመቀበል ለሰላም፣ ለልማትና ዴሞክራሲ መስራት ይጠበቅብናል ሲሉ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ ገለጹ። በሲዳማ ክልል 18ኛው የኢትዮጵያ ብሔር ብሔረሰቦችና ህዝቦች ቀን በዓል ክልላዊ ማጠቃለያ መርሃ ግብር በተለያዩ ዝግጅቶች በሀዋሳ ከተማ ተከናውኗል ።   በመርሀ ግብሩ ላይ የተገኙት የሲዳማ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ፣ ብዝሃነትን እንደ ፀጋ መቀበል ለሰላም፣ ለልማትና ዴሞክራሲ መሠረት ሲሆን ለህብረብሔራዊነትና ለጋራ ሀገራዊ ራዕይ ግንባታ መሳሪያ መሆኑንም ተናግረዋል። ''ብዝሃነታችንን እንደ ፀጋ በመጠቀም በአንድነትና በወንድማማችነት ኢትዮጵያን ለማሳደግ በትጋት መሥራት ይጠበቅብናል'' ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል። በዓሉ በክልል ደረጃ ከመጠቃለሉ በፊት በወረዳና ከተማ አስተዳደሮች ባሉ በተለያዩ አደረጃጀቶችና በትምህርት ቤቶች መከበሩን ጠቅሰዋል ። በዓሉ በርካታ ማህበረሰብን የሚጠቅሙ በጎ ተግባራት በማከናወን መከበሩን አስታውሰው የደም ልገሳ፣ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎች፣ የከተማ ፅዳትና ውበት ሥራ እንዲሁም የማዕድ ማጋራት ተግባራት መከናወናቸውን አስረድተዋል። ከበዓሉ ተሳታፊዎች መካከል አቶ በቀለ ፍሰሀ፣ ''ከዚህ በፊት ልዩነቶቻችንን እንደ ውበትና አቅም የመመልከት ክፍተቶች ይታዩ ነበር'' ብለዋል። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ህብረብሔራዊነት ላይ ያተኮረ የፌዴራል ሥርዓት ለመገንባት ጥረት እየተደረገ መሆኑን ማየታቸውን ጠቅሰዋል ። ወይዘሮ ምንትዋብ ገብረመስቀል በበኩላቸው ''ብዝሃነታችን ዛሬ የተፈጠረ ሳይሆን ከጥንት ጀምሮ አብሮን የኖረ የፈጣሪ ፀጋ ነው'' ብለዋል ። ''ይህንን ፀጋችንን እንደ መልካም ዕድል በመጠቀም ተከባብረንና ተደጋግፈን በመስራት ጠንካራ ሀገር መገንባት ይገባናል'' ነው ያሉት ። በማጠቃለያ መርሃ ግብሩ ላይ ከፌዴራልና ከአጎራባች ክልሎች የተወከሉ የሥራ ኃላፊዎች የተገኙ ሲሆን ከሲዳማ ክልል፣ ከዞኖች፣ ከወረዳና ከተማ አስተዳደሮች የተውጣጡ አመራሮችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል ።  
የፌደራል ሥርዓቱ በጽኑ መሰረት ላይ ለመገንባት ሁሉም የድርሻውን መወጣት አለበት
Dec 2, 2023 97
አዲስ አበባ፤ ህዳር 22/2016(ኢዜአ)፡-የብሔር ብሔረሰቦች በዓል የፌደራል ሥርዓቱን በጽኑ መሰረት ላይ ለመገንባት ከፍተኛ ሚና እንዲኖረው ማድረግ ከሁላችንም የሚጠበቅ ተግባር ነው ሲሉ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባዔ ዘሃራ ዑመድ ገለጹ። 18ኛው የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን ዛሬ በአዲስ አበባ ተከብሯል።   በመድረኩ የብሔር ብሔረሰቦች ቀን መከበር ያለው ጠቀሜታና የፌዴራሊዝም ምንነትና ባህሪያትን የሚዳሰሱ ጽሁፎች ቀርበው ውይይት ተካሂዷል። የፌዴሬሽን ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባዔ ዘሃራ ዑመድ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ የበዓሉ መከበር ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦችን የመቻቻልና የመከባበር ባህልን ይበልጥ ያዳብራል። በሕዝቦች መካከል እምቅ ባህላዊ እሴቶች በመገንባትና በፌዴራል ሥርዓቱ የዳበረውን አንድነት ከትውልድ ወደ ትውልድ በቅብብሎሽ እንዲሸጋገር ከፍተኛ አስተዋፅዖ ያበረክታል ብለዋል። በዓሉ ሲከበር ብዝኃነትን በማስተናገድና ሕብረ-ብሔራዊ ኢትዮጵያን በማጠናከር አገራዊ አንድነትን ማስጠበቅ ላይ ትኩረት መደረጉን ጠቅሰው ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት። ስለዚህም የብሔር ብሔረሰቦች በዓል የፌደራል ሥርዓቱን በጽኑ መሰረት ላይ ለመገንባት ከፍተኛ ሚና እንዲኖረው ማድረግ ከሁላችንም የሚጠበቅ ተግባር ነው ሲል ጥሪያቸውን አቅርበዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ቡዜና አልከድር በበኩላቸው፤ የበዓሉ መከበር የብሔር፣ የቋንቋ፣ የባህልና የሃይማኖት ማንነቶች ዕውቅና እያገኙ እንዲሄዱ ያስችላል ብለዋል።   በዓሉ ማንነቶችን እርስ በእርስ ለማስተዋወቅ እድል ከመስጠቱ ጎን ለጎንም እነዚህን ልዩነቶች በማቻቻል አገራዊ አንድነትን ለማጠናከርም ትልቅ አስተዋጽዖ ማበርከቱን ነው የገለጹት። በመድረኩ የመወያያ ጽሁፍ ያቀረቡት በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር ፈትሂ መህዲም የበዓሉ መከበር አንደኛው የሌላኛውን ባህልና እሴት እንዲያውቅ ያግዛል ብለዋል። እንዲሁም በህዝቦች መካከል ጠንካራ የሆነ ትስስር በመፍጠር ሕብረ-ብሔራዊ ኢትዮጵያን ለመፍጠር ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል ነው ያሉት። የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው ኢትዮጵያ ህብረ-ብሔራዊ አገር መሆኗን በመገንዘብ እርስ በእርስ በመደጋገፍ ችግሮቻችን በጋራ መቅረፍ አለብን ብለዋል። 18ኛው አገር አቀፍ የኢትዮጵያ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በፌዴሬሽን ምክር ቤት አስተባባሪነትና በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት አስተናጋጅነት «ብዝኃነትና እኩልነት ለአገራዊ አንድነት» በሚል መሪ ኃሳብ በጅግጅጋ ከተማ ይከበራል።
ስልጠናው አንድነቷ የተጠበቀና ሰላሟ የተረጋገጠ ኢትዮጵያን ለመገንባት አቅም የፈጠረ ነው-የስልጠናው ተሳታፊዎች
Dec 2, 2023 66
ባህር ዳር፤ ህዳር 22/2016 (ኢዜአ)፦ ለመንግስት አመራር አባላት እየተሰጠ ያለውን ስልጠና እየተከታተሉ ያሉ ሰልጣኞች ስልጠናው አንድነቷ የተጠበቀና ሰላሟ የተረጋገጠ ኢትዮጵያን ለመገንባት አቅም የፈጠረ መሆኑን የስልጠናው ተሳታፊዎች ገለጹ። በባህር ዳር የስልጠና ማዕከል “ከእዳ ወደ ምንዳ” በሚል መሪ ሃሳብ እየተሰጠ የሚገኘው 4ኛ ዙር የመንግስት አመራሮች ስልጠና ቀጥሏል።   የስልጠናው ተሳታፊ ወይዘሮ አስረሳሽ ኩምሳ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያ አሁን ከገጠማት ችግር ለመውጣት የአመራሩ አቅም ግንባታ ስልጠና ለውጥ የሚያመጣ ነው። ''ስልጠናው ገዥና የወል ትርክቶች ላይ አተኩሮ በመስራት አገራችንን ወደ ብልጽግና ጉዞ ማሻገር የሚያስችል አቅም የፈጠረ ነው '' ብለዋል። እንዲሁም ወንድማማችነትንና እህትማማችነትን አጠናክሮ በማስቀጠል በህብረ ብሄራዊ አንድነት ኢትዮጵያን ለመገንባት ፋይዳው የጎላ መሆኑን ተናግረዋል። ሌላው የስልጠናው ተሳታፊ አቶ ደጀኔ ጤና በበኩላቸው፤ ስልጠናው ከሁሉም የኢትዮጵያ አካባቢዎች የመጡ አመራሮች በአንድ ስፍራ እውቀትና ክህሎትን የሚገበያዩበት በመሆኑ የተለየ ያደርገዋል ብለዋል።   ይህም የህዝቡን አብሮነት፣ ወንድማማችነት፣ መተሳሰብ፣ መረዳዳትና መደጋገፍ በማስቀጠል አገሪቷ የገጠሟትን ችግሮች በጋራ ለመፍታት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በእያንዳንዱ ክልል ያለው ችግር ሁሉም አመራር እንዲረዳው በማድረግ በቀጣይ በጋራ በመቆም መፍትሄ ለመስጠት የሚያስችል አቅም እየተገነባበት ያለ ስልጠና መሆኑን አስረድተዋል። በተጨማሪም ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ አመራሮች ልምድና ተሞክሮ ለመቀያየር እድል የሰጠ በመሆኑ በቀጣይ መጠናከር ያለበት ጉዳይ ነው ሲሉም ገልጸዋል።   "በስልጠናው ዘላቂ ተጠቃሚነትንና የአገር አንድነትን እንዴት አጠናክረን ማስቀጠል አለብን የሚል ግንዛቤ ያገኘሁበት ነው" ያሉት ደግሞ አቶ አብርሃም አምቾ ናቸው። ''በተለይም በአርቴፍሻል ኢንተለጀንስ ላይ የተሰጠው ስልጠና ግብርናን፣ ጤናን፣ ፋይናንስን፣ ገቢ መሰብሰብንና ሌሎች የኢኮኖሚ ልማት ስራዎችን ቴክኖሎጂን በመጠቀም ማሳለጥ እንደሚገባ እውቀት የያዝንበት ነው'' ብለዋል። በተጨማሪም የመንግስትን አሰራር በቴክኖሎጂ በማስደገፍ ሙስናን እንዴት መከላከል እንደሚቻልና ጊዜን በአግባቡ በመጠቀም ለህዝቡ የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት አቅም የፈጠረ መሆኑንም ገልጸዋል። በባህር ዳር የስልጠና ማዕከል ''ከእዳ ወደ ምንዳ'' በሚል መሪ ሀሳብ ከአንደኛ እስከ 3ኛ ዙር ስልጠና ሲሰጥ ቆይቷል።  
ወይዘሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ እና አቶ ታደሰ ለማ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ዕጩ ሰብሳቢ ሆነው ቀረቡ
Dec 2, 2023 122
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 22/2016(ኢዜአ)፦ወይዘሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ እና አቶ ታደሠ ለማ የብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢነት ዕጩ ሆነው ቀረቡ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ስምንት አባላት ያሉት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ዕጩ መልማይ ኮሚቴ መሰየማቸው ይታወሳል። የኮሚቴው ሰብሳቢ ቀሲስ ታጋይ ታደለን ጨምሮ የኮሚቴው አባላት በተገኙበት የእስካሁን ክንውኖቹን አስመልክቶ ኮሚቴው ዛሬ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል። ኮሚቴው ባደረገው የጥቆማ መቀበል ሂደት ከደረሱት 52 ወንዶች፣ 4 ሴቶች በድምሩ 56 ሰዎች ጥቆማዎች መካከል በሶስት ደረጃዎች የማጣራት ሂደት ለመጨረሻ ዙር አምስት ዕጩዎች መለየታቸው ተገልጿል። ከ5ቱ መካከልም ኮሚቴው በተቀመጡ መስፈርቶች መሰረት ሁለቱን ለመጨረሻ ዙር ለይቶ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድ እንዲቀርቡ በሙሉ ድምፅ መወሰኑን አስታውቋል። በዚህም ወይዘሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ አበባው እና አቶ ታደሠ ለማ ገርቢ መስፈርቱን አሟልተው መለየታቸውን ኮሚቴው ገልጿል። በኢትዮጵያ ነጻ፣ ፍትሃዊና ታአማኒነት ያለው ምርጫ ለማካሄድ ይረዳ ዘንድ የዕጩ ሰብሳቢ ልየታ ሂደቱ ብርቱ ጥንቃቄ የተደረገበት እና ኮሚቴው ቀን ከሌሊት በትኩረት የሰራበት ስለመሆኑም ተገልጿል። የስነ-ምግባር እና የፖለቲካ ተሳትፎ ገለልተኝነት ከምልመላ መስፈርቶች መካከል እንደሆኑ ኮሚቴው አብራርቷል። ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ከቀረቡ ሁለቱ ዕጩዎች መካከል አንድ የምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ዕጩ በፓርላማ ቀርቦ የሚሾም ይሆናል። በመግለጫ ላይ እንደተጠቆመው በትምህርት ደረጃ ረገድ ወይዘሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ በሕግ የመጀመሪያ ዲግሪ፣ በሰላምና ደህንነት ጥናት ሁለተኛ ዲግሪ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እንዲሁም በህዝብ አስተዳደር ተጨማሪ ማስተርስ ዲግሪ ከሀርቫርድ ዩኒቨርሲቲ ተቀብለዋል። በስራ ልምድ ረገድ በኢትዮጵያ ጉምሩክ ባለስልጣን ለስምንት ዓመታት፣ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የፅህፈት ቤት ሃላፊነት ሆነው ለሁለት ዓመታት አገልግለዋል። በተመሳሳይ አቶ ታደሠ ለማ የመጀመሪያ ዲግሪ በእንግሊዘኛ ቋንቋ ከባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ፣ ሁለተኛ ዲግሪ በዓለም አቀፍ ግንኙነት ከወለጋ ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ዝግጅት እንዳላቸው ተገልጿል። አቶ ታደሰ ካላቸው ልምድ መካከል በምርጫ ቦርድ የቤኒሻንጉል ጉምዝ ምርጫ ክልል ሃላፊ ሆነው መምራታቸው ተወስቷል።    
የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በአዲስ አበባ እየተከበረ ነው
Dec 2, 2023 76
አዲስ አበባ ፤ ህዳር 22/2016(ኢዜአ)፡- ለ18ኛ ጊዜ የሚከበረው የብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በአዲስ አበባ ከተማ በተለያዩ ሁነቶች እየተከበረ ይገኛል። ''ብዝኃነት እና እኩልነት ለሀገራዊ አንድነት'' በሚል መሪ ቃል በአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አስተባባሪነት ከተማ አቀፍ የማጠቃለያ የፓናል ውይይት እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባዔ ዘሃራ ዑመድ፣ የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባዔ ቡዜና አልከድር እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።   በመድረኩ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የፌዴሬሽን ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባዔ ዘሃራ ዑመድ እንዳሉት፤ የበዓሉ መከበር ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ሊኖራቸው የሚገባው የመቻቻልና የመከባበር ባህልን ይበልጥ ያዳብራል። በሕዝቦች እምቅ ባህላዊ እሴቶች እየተገነባና በፌዴራል ሥርዓቱ የዳበረውን አንድነት ከትውልድ ወደ ትውልድ በቅብብሎሽ እንዲሸጋገር ከፍተኛ አስተዋፅዖ እንደሚያበረክት አመላክተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ቡዜና አልከድር በበኩላቸው፤ የበዓሉ መከበር የአገሪቱ ውበት የሆኑ የብሔር፣ የቋንቋ፣ የባህል እንዲሁም የሃይማኖት ማንነቶች መኖራቸው ዕውቅና እያገኘ እንዲሄድ አድርጓል ነው ያሉት። እነዚህን ልዩነቶች በማቻቻልና አንድነትን በማጠናከር ከጊዜ ወደ ጊዜ ብዙኃኑ የሚስማማበት አስተሳሰብ እየሆነ እንዲመጣ አስችሏል ብለዋል፡፡ የበዓሉ መከበር በመፈቃቀድ ታላቋን ኢትዮጵያ የገነቡትን ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ከውብ ባህላቸው ለመተዋወቅ እና ለልዩ ልዩ ማንነቶች ዕውቅና በመስጠት፣ የመገለልና የመጨቆን ስሜቶችን በማስወገድ አገራዊ አንድነትን ያጠናክራል ብለዋል። 18ኛው አገር አቀፍ የኢትዮጵያ ብሔር፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በፌዴሬሽን ምክር ቤት አስተባባሪነትና በሶማሌ ክልላዊ መንግሥት አስተናጋጅነት «ብዝኃነትና እኩልነት ለሀገራዊ አንድነት» በሚል መሪ ቃል በጅግጅጋ ከተማ ይከበራል።      
በመከላከያ ሠራዊቱና በህዝቡ ቅንጅት አንፃራዊ ሠላም ማምጣት ተችሏል- ሌተናል ጀኔራል ሹማ አብደታ
Dec 2, 2023 74
አዲስ አበባ፤ ህዳር 22/2016(ኢዜአ)፦መከላከያ ሠራዊቱ እና ህዝቡ ተቀናጅተው በመሥራታቸው በአካባቢው አንፃራዊ ሠላም ማምጣት ተችሏል ሲሉ የኮማንዶና አየር ወለድ ዕዝ አዛዥና የማዕከላዊ ሸዋ ዞን ኮማንድ ፖስት ሰብሳቢ ሌተናል ጀነራል ሹማ አብደታ ገለጹ። በከሚሴ ከተማ በአካባቢው ፀጥታና ሰላም ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ህዝባዊ ውይይት ተካሂዷል፡፡   ሌተናል ጀነራል ሹማ ከአፋር ክልል ዞኖች፣ ከአማራ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን እና ከኦሮሞ ብሔረሰብ ዞን ከተወጣጡ የዞን፣ የከተማ፣ የወረዳና ቀበሌ አስተዳደሮች እንዲሁም ከኃይማኖት አባቶች፣ ከሀገር ሽማግሌዎች እና ከፀጥታ ኃይሎች ጋር በሰላምና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ ተወያይተዋል፡፡ በዚህ ወቅት ሌተናል ጀነራል ሹማ የሀገር መከላከያ ሠራዊቱ እና ህዝቡ ተቀናጅተው በመስራታቸው በአካባቢው አንፃራዊ ሰላም መስፈን መቻሉን ገልፀው፤ ያለጠንካራ አንድነት ጠንካራ ሀገር አይኖርምና ለጋራ አላማ በጋራ በመሰለፍ የበለፀገች ኢትዮጵያን ለመፍጠር የሚጠበቅብንን መወጣት አለብን ብለዋል።   የዞን አስተዳዳሪዎች በበኩላቸው መከላከያ ሠራዊት ሀገርን ለማሻጋር ዋጋ እየከፈለ እንዳለው ሁሉ እኛም ከጎኑ ሆነን የሚጠበቅብንን በመወጣት ኢትዮጵያን በጋራ እንጠብቃታለን ሲሉ ተናግረዋል። የረከሰ አስተሳሰብ ይዘው ህዝብ ውስጥ በመመሸግ በደም ለመነገድ የሚጥሩ ፅንፈኛ ሃይሎችን ተከታትለን ለህግ በማቅረብ የመከላከያ ሠራዊቱ እና የፀጥታ ሃይሉ አጋዥ ሆነን እንቀጥላለንም ብለዋል። የውይይቱ ተሳታፊዎች የአከባቢው ህብረተሰብ ከጥንት ጀምሮ በጋብቻ፣ በባህል፣ በእምነት ተጋምዶ በሀዘንና በደስታ አብሮ የኖረ አሁንም አብሮ ያለ መሆኑን ገልፀው እኔ አውቅልሃለው ባይ ህገ ወጦች የፈጠሩትን ችግር እንደሚያወግዙ እና ከሠራዊቱ ጋር እንደሚሠሩ መናገራቸውን ከመከላከያ ሰራዊት ማህበራዊ ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።            
የሲቪክ ማኅበራት በዴሞክራሲ ሥርዓት ውስጥ ያላቸው ሚና ለማጎልበት በትኩረት እየተሰራ ነው
Dec 1, 2023 66
አዲስ አበባ፤ ህዳር 21/2016(ኢዜአ)፦ የሲቪክ ማኅበራት በዴሞክራሲ ሥርዓት ውስጥ ያላቸው ሚና እንዲጎለብት የውይይትና የምክክር መድረኮች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተገለጸ። የአዲስ አበባ ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ከሲቪክ ማኅበራት ተወካዮችና ባለድርሻ አካላት ጋር "የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ የባለድርሻ አካላት ሚና" በሚል ርዕስ የውይይት መድረክ ዛሬ አካሂዷል።   በውይይት መድረኩ የሲቪክ ማኅበራትና ባለድርሻ አካላት በኢትዮጵያ የዳበረ ዴሞክራሲን ለመገንባት በውይይትና በምክክር ሚናቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ያለመ ነው። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የዴሞክራሲ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ ሃላፊ ሞገስ ባልቻ እንደገለጹት የሲቪክ ማኅበራት በዴሞክራሲ ሥርዓትና ባህል ግንባታ ሂደት ውስጥ ያላቸው ጉልህ ሚና ከፍተኛ ነው። ሲቪክ ማኅበራት በዴሞክራሲ ሥርዓትና ባህል ግንባታ ድርሻቸውን ማበርከት የሚችሉት በጋራ ምክክርና ውይይት የሃሳብ ገበያ ሲፈጥሩ መሆኑን አመልክተዋል። የሲቪክ ማኅበራትና ባለድርሻ አካላት ዴሞክራሲው እንዲያብብ ሰላማዊ የሃሳብ ትግልን ማጠናከር እንደሚጠበቅባቸው ጠቁመዋል። ዴሞክራሲ በአንድ ጊዜ ተጀምሮ በአንድ ጊዜ የሚጠናቀቅ ሳይሆን በተቋማት ግንባታና በማኅበረሰብ የአስተሳሰብ ለውጥ ሲረጋገጥ ነው ብለዋል። ዴሞክራሲ መሠረት የሚይዘው አስተማማኝና ጠንካራ በሆኑ ዴሞክራሲን የሚያለመልሙ ተቋማት ሲዘረጉና ሲገነቡ መሆኑንም አውስተዋል። የዴሞክራሲ ግንባታ በተቋማት እንቅስቃሴ ጭምር የሚሳካ በመሆኑ ይህም እውን ለማድረግ በርካታ ተግባራት እየተከናወነ መሆኑን አመልክተዋል። የሲቪክ ማኅበራት በዴሞክራሲ ሥርዓት ውስጥ ያላቸው ሚና እንዲጎላ የውይይትና የምክክር መድረኮች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በአዲስ አበባ ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ሃላፊ የኋላሸት በቀለ በበኩላቸው ዴሞክራሲው እንዲጎለብት ውይይቱና ምክክሩ ተጠናክሮ እንዲቀጥል መግባባት ላይ መደረሱን ገልጸዋል። የዴሞክራሲ ግንባታ ሂደት እንዲጎለብት አካታችነት ባለው መልኩ የተለያዩ የውይይት መድረኮች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጸዋል። የውይይት መድረክ ተሳታፊዎችም የዳበረ ዴሞክራሲ ለመገንባት የተጀመረው ውይይት ይበልጥ ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል።  
የኢትዮጵያውያን የአብሮነት መስተጋብር እሴቶች እንዲጎለብቱ መሥራት ይገባናል-ርዕሰ መስተዳድር ኦርዲን በድሪ 
Dec 1, 2023 61
ሐረር፤ ህዳር 21/2016 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያውያን የአብሮነትና የአዎንታዊ መስተጋብር እሴቶች እንዲጎለብቱ መሥራት ይገባናል ሲሉ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ አስገነዘቡ። በሐረር ከተማ 18ኛው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በዓል በድምቀት ተከብሯል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኦርዲን በድሪ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት “የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በዓል ኢትዮጵያ የብዝሃነት አገር መሆኗን በተጨባጭ የሚያሳይ ነው።'' በዓሉ የተለያየ ቋንቋ፣ ባህልና ታሪክ ያላቸው የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች አንድነታቸውን ያጠናከሩበት መሆኑንም አመልክተዋል። በተጨማሪም ዘላቂ ሰላምና ልማትን ለማረጋገጥ እያገዘ መሆኑን ርዕሰ መስተዳድሩ ያስታወቁት። አቶ ኦርዲን እንዳሉት የክልሉ መገለጫ የሆኑ የአንድነት፣ የአብሮነትና የአዎንታዊ መስተጋብር እሴቶች እንዲጎለብቱ ቀጣይነት ያላቸው ሥራዎች ማከናወን ይገባል። "የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች በማህበራዊ መስተጋብሮቻችን ያለንን አንድነት በማጠናከር ለሀገር ብልጽግና መሥራት ይገባናል" ሲሉም ተናግረዋል። በክልሉ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለማቃለልና ለሕዝብ ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ትኩረት ሰጥቶ መስራት እንደሚገባም አሳስበዋል። በተጨማሪም በተቋማት የሚታዩ ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን በማስወገድ በዓሉ ያስገኘውን ትሩፋት ማስቀጠል ይገባል ሲሉ አስገንዝበዋል። የክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ ሱልጣን አብዱሰላም በበኩላቸው የዘንድሮ የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ቀን በዓል “ብዝሃነትና እኩልነት ለአገራዊ አንድነት!'' በሚል ቃል በክልሉ በልማትና በተለያዩ ዝግጅቶች ሲከበር መቆየቱን አስታውሰዋል። ኅዳር 29 ለኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች እውቅና የሰጠ ሕገ መንግሥት የፀደቀበት ዕለት መሆኑን ያስታወሱት አፈ ጉባዔው፤ በዓሉ የኢትዮጵያውያንን አንድነት ያጠናከረና እርስ በእርስ ያስተሳሰረ ነው ብለዋል፡፡ በዓሉ የህዝቦች የእኩልነት መብት በሕገ መንግሥት የተረጋገጠበት መሆኑን አስታውሰው፣ የክልሉ ሕዝብ በጅግጅጋ ከተማ በሚከበረው በዓል ላይ የሚታደሙ እንግዶችን ተቀብሎ እንዲያስተናገድም አስገንዝበዋል። በበዓሉ የተሳተፉት አቶ ቶፊቅ መሐመድና ወይዘሮ ነቢላ መሐመድ በበኩላቸው አብሮነትንና አንድነትን በማጠናከር በክልሉ የተጀመሩ የሰላምና የልማት ሥራዎችን ለማስቀጠል ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል። የክልሉን ሕዝብ የልማት ጥያቄዎችን በተሻለ ለመመለስና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት ትኩረት ተሰጥቶ እንዲሰራም ጠይቀዋል። አገራዊ አንድነት የሰፈነባት የተሻለች ኢትዮጵያን መፍጠር በሚያስችል መልኩ በዓሉን ማክበር እንደሚገባም ተናግረዋል። በሥነ-ሥርዓቱ ላይ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ሃላፊዎች፣ የኃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎችና ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች ታድመዋል።    
የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን የኮሙኒኬሽን ስትራቴጂ ሰነድ እያዘጋጀ ነው
Dec 1, 2023 71
አዲስ አበባ፤ ህዳር 21/2016 (ኢዜአ)፦ የኢፌዴሪ ብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን የቀድሞ ተዋጊዎችን መልሶ ለማቋቋም የሚያደርገው ጥረት ውጤታማ እንዲሆን ለማስቻል የኮሙኒኬሽን ስትራቴጂ ሰነድ እያዘጋጀ ነው። የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን ያዘጋጀውን ረቂቅ የኮሙኒኬሽን ስትራቴጂ ሰነድ በተመለከተ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አድርጓል። ኮሚሽነር አምባሳደር ተሾመ ቶጋ በዚሁ ጊዜ እንደገለጹት፤ የቀድሞ ተዋጊዎችን መልሶ ለማቋቋም የሚሰሩ ሥራዎችን ውጤታማ ለማድረግ የኮሙኒኬሽን ስትራቴጂ ረቂቅ ሰነድ ተዘጋጅቷል። ይህም ወቅታዊ፣ ግልጽና ቀልጣፋ መረጃዎችን የመለዋወጫ ምህዳር ለማስፋት ያስችላል ነው ያሉት። የኮሙኒኬሽን ስትራቴጂ ሰነዱ በተለይም ኮሚሽኑ ለተለያዩ ባለድርሻና አጋር አካላቶች የሚያስተላልፋቸውን መረጃዎች በምን መልኩና ለማን ምን አይነት መረጃ መቅረብ አለበት የሚለውን ለማመላከት ወሳኝ ነው ብለዋል። በቀጣይ ኮሚሽኑ የኮሙኒኬሽን ስትራቴጂ ሰነዱን ከዘርፉ ተዋናዮች የሚሰጡት ገንቢ ሃሳቦች በማዳበር ሥራ ላይ እንደሚውል ጠቁመዋል። የብሔራዊ ተሃድሶ ኮሚሽን ጽህፈት ቤት ሃላፊ ሻንቆ ደለለኝ በበኩላቸው የኮሙኒኬሽን ስትራቴጂ ሰነዱ የቀድሞ ተዋጊዎች ወደ ማኅበረሰቡ ሲቀላቀሉ በማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ ተሳታፊ እንዲሆኑ የማኅበረሰቡን ግንዛቤ ለማስጨበጥ ሰፊ እድል እንዳለው ገልጸዋል። የቀድሞ ተዋጊዎችን መልሶ ለማቋቋም ትልቅ ሃብትን የሚጠይቅ በመሆኑ አጋር አካላቶች በዚህ ላይ ያላቸውን ተሳትፎ ለማጠናከር የኮሙኒኬሽን ስትራቴጂ ሰነዱ ጠቀሜታ እንደሚኖረውም አመላክተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም