ቀጥታ፡
ፖለቲካ
ሰባተኛውን ሀገራዊ ጠቅላላ ምርጫ ፍትሐዊ እና ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ ማከናወን የሚያስችል ዝግጅት ተደርጓል
Jan 13, 2026 89
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ ሰባተኛውን ሀገራዊ ጠቅላላ ምርጫ ፍትሐዊ እና ዲሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ ማከናወን የሚያስችል ዝግጅት መደረጉን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ገለጹ። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሀገር አቀፍ የሕግ አውጪዎች የጋራ ምክክር መድረክ በቢሾፍቱ ከተማ እየተካሄደ ነው።   የጋራ የምክክር መድረኩ የመንግሥታት ግንኙነት ስርዓትን ለመወሰን በወጣው አዋጅ ቁጥር 1231/2013 መሰረት ይካሄዳል። በፌዴራል መንግሥት ፖሊሲዎች ሕጎችና ስትራቴጂዎች ላይ ተቀራራቢ አፈፃፀም፣ የጋራ መግባባት፣ ማሕበራዊ ፍትህ፣ ዘላቂ ሰላምና መልካም አስተዳደር፣ ዲሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብት ጥበቃ እንዲሁም አንድ የፖለቲካ ማህበረሰብ ለመገንባት ያለመ ነው። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ በዚህ ወቅት፣ ሀገር አቀፍ የሕግ አውጪዎች የጋራ ምክክር መድረክ ዘላቂ ሰላምና ልማትን በማረጋገጥ የአንድ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማህበረሰብ ለመገንባት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በዘንድሮው የምክክር መድረክ ወቅታዊና ሀገራዊ ጉዳዮች ተነስተው ከፌደራልና ከክልል ህግ አውጪዎች ጋር ውይይት ይደረግባቸዋል ብለዋል። ሰባተኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ ዝግጅትና የምክር ቤቶች ሚና፣ የፐብሊክ በጀትና የፋይናንስ ትንተና እና ጥናት ሰነድ እንዲሁም የሕግ ኦዲት ሰነድ ላይ ምክክር እንደሚደረግም ገልጸዋል። መንግስት ሰባተኛው ሀገራዊ ጠቅላላ ምርጫ አስቻይ ሁኔታዎችን ለመፍጠር የግብዓት አቅርቦትና ሚና በተመለከተ ምክክር ማድረጉን ተናግረዋል።   የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትና የክልል ምክር ቤቶች የዘንድሮው ምርጫ ከስድስተኛው ጠቅላላ ምርጫ በተሻለ እንዲፈጸም የማስተባበር ሚናችንን በብቃት መወጣት አለብንም ነው ያሉት። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በርካታ ሪፎርሞች ማድረጉን በማንሳት፤ የክትትልና ቁጥጥር፣ የህዝብ ውክልና ሥራ በብቃት መወጣት የሚያስችል ሥራ እያከናወነ መሆኑንም አክለዋል። በዚህም ምክር ቤቱ የህግ ማዕከል በማቋቋም የሚወጡ ህጎች ከህገ መንግስቱ፣ ከዓለም አቀፍ ህጎች እና ቀድመው ከነበሩ ሀገራዊ ህጎች ጋር የተጣጣሙ መሆናቸውንና ተፈፃሚነታቸውን መከታተል የሚያስችል አሰራር ተዘርግቷል ብለዋል። የሀገር አቀፍ የሕግ አውጪዎች የጋራ የምክክር መድረክ የጋራ ትርክትን መገንባትና ግልፅነትን መፍጠር የሚያስችል ምህዳር ማስፈን እንደሚያስችል ጨምረው ገልጸዋል።
የጋራ ትርክት መገንባት ለነገው ትውልድ የምትመች ሀገር መፍጠር ማለት ነው
Jan 12, 2026 120
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ የጋራ ትርክት መገንባት ለነገው ትውልድ የምትመች ሀገር መፍጠር ማለት መሆኑን አምባሳደር ሌንጮ ባቲ ገለጹ። በኢትዮጵያ የጋራ ሀገራዊ ትርክቶችን ለመቅረጽ ያለመ ኮንፍረንስ በጅማ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።   አምባሳደር ሌንጮ ባቲ በኮንፍረንሱ ባቀረቡት የመወያያ ጽሑፍ የጋራ ትርክት መገንባት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። ልዩነቶችን በጠረጴዛ ዙሪያ በማምጣት መወያየትና መነጋገር እንደሚገባ ጠቁመው፤ ምክክር ማድረግ ሁነኛ አማራጭ ነው ብለዋል። አንድነትን፣ አብሮነትንና እኩልነትን የሚያጎላ ትርክት መቅረጽ እንደሚገባም ተናግረዋል።   የሚያስተሳስሩ እና ዘመን ተሻጋሪ አብሮነቶችና ትስስሮችን ማጉላት የሚያስችል ትርክትን መገንባት እንደሚገባም ገልጸዋል። የጋራ ትርክት መገንባት ለነገው ትውልድ የምትመችና የበለጸገች ኢትዮጵያን መፍጠር መሆኑንም አንስተዋል።   "ሀገራዊ ማንነት፣ የጋራ ትውስታዎችና የሀገረ መንግሥት ቅቡልነት፤ የኢትዮጵያ ተሞክሮ እና የመገናኛ ብዙኃን ሚና" በሚል ርዕስ ጽሑፍ ያቀረበችው ሙኒራ አብዱልመናን መገናኛ ብዙኃን የሀገረ መንግሥት ግንባታ ሂደትን በማሳለጥና የዜጎችን የጋራ ማንነት በመቅረጽ ረገድ የጀርባ አጥንት መሆናቸውን ተናግራለች። መገናኛ ብዙሃን ከአግላይና ነጣጣይ ትርክቶች ይልቅ የወል ትርክቶችን እና እሴቶችን ማጉላት እና ማስተጋባት እንደሚገባቸው ገልጻለች። መገናኛ ብዙኃን ለብሔራዊ መግባባት ቅድሚያ ሊሰጡ እንደሚገባም ጨምራ ተናግራለች። የመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎችም ስለ ሀገረ መንግሥት ግንባታ ያላቸው ግንዛቤ ሊያድግ እንደሚገባ በመግለጽ፤ ለትውልድ የሚሻገር አስተሳሳሪ ትርክት ለመገንባት መትጋት እንደሚገባቸውም አንስታለች። በመድረኩ በኢትዮጵያ የጋራ ትርክትን ተቋማዊ ለማድረግ በሚቻልባቸው መንገዶች ላይ ሰፊ ውይይት እየተካሄደ ይገኛል።
በጋምቤላ ክልል የህግ የበላይነትን በማስከበር የልማት ስራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ ነው - ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ
Jan 12, 2026 98
ጋምቤላ፤ ጥር 4/2018(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል የህግ የበላይነትን በማስከበር የልማት ስራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ ገለጹ። የጋምቤላ ክልል የመንግስት ሰራተኞች በክልሉ ወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ በጋምቤላ ከተማ የውይይት መድረክ አካሂደዋል። በውይይት መድረኩ የተገኙት ርዕሰ መስተዳድር ዓለሚቱ ኡሞድ፤ በክልሉ የህግ የበላይነትን በማስከበር የልማት ስራዎችን ይበልጥ ለማጠናከር የተቀናጀ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህ ሂደት የመንግስት ሰራተኞች ተሳትፎ እና ትብብር ወሳኝ መሆኑን አንስተው በሁሉም ረገድ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ማስቀጠልና የአገልግሎት አሰጣጥን ይበልጥ ፈጣንና ቀልጣፋ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል። የሚነጣጥሉ እሳቤዎችን በመተው አሰባሳቢና የወል ትርክቶችን በመገንባት ረገድም የመንግስት ሰራተኞች የላቀ ሚናቸውን መወጣት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የክልሉን ሰላም ለማደፍረስ የሚጥሩ አካላትን በመከታተል በህግ ተጠያቂ የማድረግ፣ የህግ የበላይነትን የማረጋገጥና የልማት ስራዎችን ለስኬት የማብቃት ጉዳይ በቀጣይ በልዩ ትኩረት ይሰራል ብለዋል።   የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር ጋትሉዋክ ሮን(ዶ/ር) የክልሉ መንግስት የህግ የበላይነትን በማረጋገጥ የልማት ስራዎችን ይበልጥ አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም የሁሉም ድጋፍና ትብብር አስፈላጊ መሆኑን አንስተው በተለይም የመንግስት ሰራተኞች የላቀ ሚናቸውን እንዲወጡ አስገንዝበዋል። በብልፅግና ፓርቲ የጋምቤላ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አሽኔ አስቲን፤ የአስተሳሰብና የተግባር አንድነትን በማጠናከር ለክልሉ ዘላቂ ሰላምና ልማት በጋራ ልንቆም ይገባል ብለዋል። የመድረኩ ተሳታፊ የመንግስት ሰራተኞችም ለክልሉ ዘላቂ ሰላምና የልማት ስራዎች መሳካት የድርሻቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። በጋምቤላ ክልል ለልማት የሚውል እምቅ የተፈጥሮ ሀብት መኖሩን አንስተው በጋራ በመስራትና በማልማት ጥቅም ላይ የማዋል ስራ እንዲሳካ እንሰራለን ብለዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
የጋራ ትርክት ለጠንካራ የሀገረ መንግሥት ግንባታና ለትውልድ ሽግግር ጉልህ ሚና አለው
Jan 12, 2026 125
አዲስ አበባ፤ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦የጋራ ትርክት ለጠንካራ የሀገረ መንግሥት ግንባታና ትውልድ ሽግግር ጉልህ ሚና እንዳለው የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ ገለጹ። በኢትዮጵያ የጋራ ሀገራዊ ትርክቶችን ለመቅረጽ ያለመ ብሔራዊ ኮንፍረንስ በጅማ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል። በኮንፍረንሱ ታዋቂው የታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ "የጋራ የወል ትርክት ግንባታ እና ፈተናዎቹ" በሚል ርዕስ የመነሻ ጽሑፍ አቅርበዋል።   በመነሻ ጽሑፋቸውም፤ ኢትዮጵያዊያን ከልዩነትና ነጣጣይ ትርክቶች ይልቅ በጋራ ትርክት ላይ በማተኮር ለጽኑ ሀገረ መንግሥት ግንባታ በትብብር ሊሰሩ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። አግላይና ነጣጣይ ትርክት ለሀገረ መንግሥት ግንባታ ፈታኝ መሆናቸውን በመጥቀስ የዜጎችን አንድነትና አብሮነት የሚያጠናክር የወል ትርክት መፍጠር እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያ የወል ትርክት ግንባታም በታሪክ ሂደት ውስጥ ያጋጠሙ ስብራቶችን በሚያርቅ አካሄድ አብሮነትን በሚያጸኑና ሁሉንም ወገኖች በሚያቅፉ የታሪክ እውነታዎች ላይ መሆን እንዳለበት ገልጸዋል። ምሁራን ታሪክን ለሀገረ መንግሥት ግንባታና ለሕዝቦች መቀራረብ እንዲውል የማድረግ ትልቅ ኃላፊነት እንዳለባቸውም አሳስበዋል።   የጋራ ትርክት ግንባታ ሂደቱንም በተሻለ የሃሳብ የበላይነት በመምራትም የተሻለችና አስተሳሳሪ ትርክት የነገሰባት ኢትዮጵያን ለትውልድ ማስተላለፍ እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። የጋራ ትርክት ግንባታ ለጠንካራ የሀገረ መንግሥት ግንባታና ለተሻለ የትውልድ ሽግግር ጉልህ ሚና እንደሚጫወት አብራርተዋል። በኮንፍረንሱ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፣ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)፣ የጨፌ ኦሮሚያ አፈ-ጉባኤ ሰዓዳ አብዱረህማን እና ሌሎች የፌዴራልና የክልል አመራሮች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።  
የመደመር መንግሥት ኢትዮጵያዊያንን የሚያስተሳስር ገዥ ትርክት ለመገንባት በልዩ ትኩረት እየሰራ ነው  
Jan 12, 2026 109
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦የመደመር መንግሥት ኢትዮጵያዊያንን የሚያስተሳስር ገዥ ትርክት ለመገንባት በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ገለጹ። በኢትዮጵያ የጋራ ሀገራዊ ትርክቶችን ለመቅረጽ ያለመ ሀገር አቀፍ ኮንፈረንስ በጅማ ከተማ እየተካሄደ ነው።   በመድረኩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) "ሀገራዊ ማንነት፣ የጋራ ትውስታዎች እና የሀገረ መንግሥት ቅቡልነት፤ የኢትዮጵያ ተሞክሮና የተያዙ አሁናዊ አቅጣጫዎች" በሚል ርዕስ የመደመር መንግሥት ሀገራዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የያዛቸውን ቁልፍ አቅጣጫዎች የሚያመላክት ጽሑፍ አቅርበዋል። በመነሻ ጽሑፋቸውም፤ ኢትዮጵያ ጥንታዊት፣ የሥልጣኔ መገኛ፣ የዳበረ የሥነ-መንግሥት ልምምድ ያላት፣ የሊግ ኦፍ ኔሽን የመጀመሪያዋ አባልና የአፍሪካ ሕብረት መሥራች መሆኗን አስረድተዋል።   በ1888 ዓ.ም የዓድዋ ድልም የነፃነት ተምሳሌትነትን የተጎናጸፈች፣ በቋንቋ፣ በባህልና በማንነት ስብጥር የታደለች ብትሆንም የሀገረ መንግሥት ቅቡልነት ችግር ሌላኛው ፈታኝ ገጽታዋ ሆኖ መቆየቱን ተናግረዋል። የኢትዮጵያዊያን የጋራ ማንነትና ትውስታ በንግድ፣ በኃይማኖት፣ በፍልሰትና በተፈጥሮ አደጋዎች መስተጋብር መፈጠሩንም አብራርተዋል የኢትዮጵያ ሀገረ መንግሥት ግንባታ ሂደት ገና ያልተጠናቀቀ በመሆኑም የተረጋጋና ቅቡልነት ያለው ሀገረ መንግሥት መገንባት የሁሉንም ተሳትፎ እንደሚጠይቅ አስገንዝበዋል። ኋላቀር የፖለቲካ ባሕል፣ የተዛባ ትርክትና ጸጋዎችን በአግባቡ አለመጠቀም ለሀገረ መንግሥት ግንባታ ቁልፍ ማነቆ ሆነው መቆየታቸውን አንስተዋል።   በዚህ መነሻነትም የመደመር መንግስት የኢትዮጵያን ሲንከባለሉ የመጡ ችግሮች በዘላቂነት እልባት ለመስጠት በግልጽ አቅጣጫ በመተለም በልዩ ትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ አስታውቀዋል። በዚህም ብሔራዊ መግባባትና ዕርቀ ሰላም፣ የብሔራዊነት ገዥ ትርክትና የሐሳብ ገበያ፣ የሃሳብ ፖለቲካና ኢትዮጵያ የመግባባት ዲሞክራሲ፣ የኢኮኖሚ ሉዓላዊነትና ሀገራዊ ብልጽግናን ለማረጋገጥ ውጤታማ ሥራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝ አብራርተዋል።  
የጋራ ትርክት ግንባታ የሕዝብን አብሮነት የሚያጠናክር የነገ ተስፋን የሚያንጽ ወሳኝ መሣሪያ ነው  
Jan 12, 2026 121
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦ የጋራ ትርክት ግንባታ ስብራትን በመጠገን የሕዝብን አብሮነት የሚያጠናክር የነገ ተስፋን የሚያንጽ ወሳኝ መሣሪያ መሆኑን በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ከፍያለው ተፈራ ገለጹ። በኢትዮጵያ የጋራ ሀገራዊ ትርክቶችን ለመቅረጽ ያለመ ሀገር አቀፍ ኮንፍረንስ በጅማ ከተማ መካሄድ ጀምሯል።   በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የጋራ ትርክት ግንባታ የሕዝብን አብሮነትና አንድነት የሚያጠናክር የነገ ተስፋ መገንቢያ መሣሪያ ነው። ነጣጣይ ትርክት ለሀገረ መንግስት ግንባታ እንቅፋት መሆኑን በመጠቆም፤ አሰባሳቢና የጋራ ትርክት ግንባታ ግን የሀገረ መንግስት ግንባታን በጽኑ መሰረት እንደሚያንጽ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ አሰባሳቢ ትርክት ግንባታ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ስብራቶችን በመጠገን ለዜጎች አብሮነትና ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ወሳኝ ዕድል መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በመደመር መንገድ በአሰባሳቢና የጋራ ትርክት ግንባታ በዜጎቿ ሕብረ-ብሔራዊ አንድነት የበለጸገች ኢትዮጵያን ለመገንባት ስኬታማ ተግባራት እየተከናወኑ እንደሚገኝ አብራርተዋል። የኢትጵያዊያንን ሕብረ ብሔራዊ ትስስር የሚያሰናስሉ ዘላቂ የአሰባሳቢ ትርክት ግንባታ ሥራዎችንም በስትራቴጂክ ፖሊስ ማስደገፍ ትኩረት የተሰጠው ወሳኝ ጉዳይ መሆኑን አስገንዝበዋል።   የዜጎችን የወል ትርክት ግንባታ በጽኑ መሰረት ለማነጽ በሚደረገው ጥረትም ምሁራንና ባለድርሻ አካላት ገንቢ ሚናቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ መልዕክት አስተላልፈዋል። የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ጀማል አባፊጣ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ አሰባሳቢና የወል ትርክት ግንባታ ለሀገረ መንግስት ግንባታ ትልቅ ፋይዳ አለው ብለዋል። በቀጣይም የኢትዮጵያዊያንን የጋራና አሰባሳቢ ትርክት ግንባታ ላይ በዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ብሔራዊ መግባባትን ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት የበኩላቸውን ገንቢ ሚና እንደሚወጡ ተናግረዋል። በኮንፍረንሱ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፣ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)፣ የጨፌ ኦሮሚያ አፈ-ጉባኤ ሰዓዳ አብዱረህማን እና ሌሎች የፌዴራልና የክልል አመራሮች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
የወል ትርክት መገንባት ለሕብረ ብሔራዊ አንድነት ወሳኝ ነው 
Jan 12, 2026 134
አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2018 (ኢዜአ)፦የወል ትርክት መገንባት ለሀገረ መንግሥት ግንባታና ለሕብረ ብሔራዊ አንድነት ወሳኝ መሆኑን የሰላም ሚኒስትር መሐመድ እድሪስ ገለጹ። በኢትዮጵያ የጋራ ሀገራዊ ትርክቶችን ለመቅረጽ ያለመ ሀገር አቀፍ ኮንፈረንስ በጅማ ከተማ መካሄድ ጀምሯል። የሰላም ሚኒስትር መሐመድ እድሪስ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር፥ የወል ትርክት ያሉ ክፍተቶችን የሚያስታርቅ፣ በብዝኃነት ውስጥ ያሉ የአብሮነት እሴቶችን ለማጎልበት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። የወል ትርክትን መገንባት ለሀገረ መንግሥት ግንባታና ለሕብረ ብሔራዊ አንድነት ወሳኝ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሩ ከፋፋይ ትርክትና እሳቤዎችን ማስወገድ እንደሚገባ ጠቁመዋል።   ኢትዮጵያ በሕብረ ብሔራዊ አንድነት ወደ ከፍታ ጉዞ መጀመሯን በማንሳት፥ ትውልዱን በጋራ ትርክት መቅረፅ እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል። ለዚህም ሁሉም ባለድርሻ አካላት አስተሳሳሪ ትርክትን ለመገንባት በቅንጅት መሥራት አለባቸው ብለዋል። ብሔራዊ መግባባትን ለማጎልበት አሁን ትክክለኛው ጊዜ ነው ያሉት ሚኒስትሩ ሀገራዊ የምክክር ሂደቱን በአግባቡ በመጠቀምና ሀሳብን በሰለጠነ መንገድ በማቅረብ ለውጤታማነቱ መረባረብ እንደሚገባ ጠቁመዋል። ታሪክን ለመማሪያነት ብቻ መጠቀም ያስፈልጋል ያሉት አቶ መሐመድ፣ ከትናንት ጠቃሚ የሆኑ የታሪክ እሴቶችን በመውሰድ ዛሬም ተደምረን የላቀ ታሪክ መሥራት ይኖርብናል ብለዋል።   በኮንፈረንሱ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፣ የመስኖና ቆላማ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)፣ የጨፌ ኦሮሚያ አፈ-ጉባኤ ሰዓዳ አብዱረህማን፣ በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ከፍያለው ተፈራ፣ ሌሎች የፌዴራልና የክልል አመራሮች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
በሰላምና በልማት ሥራዎች ላይ በንቃት በመሳተፍ የበደልነውን ህዝብ ለመካስ ተዘጋጅተናል
Jan 11, 2026 164
ደብረብርሃን፤ጥር 3/2018 (ኢዜአ)፡-በሰላምና ልማት ሥራዎች ላይ ንቁ ተሳትፎ በማድረግ የበደልነውን ህዝብና መንግስት ለመካስ ተዘጋጅተናል ሲሉ በሰሜን ሸዋ ዞንና በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር የሰላም አማራጭን የተቀበሉ የቀድሞ ታጣቂዎች ገለጹ። በአማራ ክልል በርካታ ታጣቂዎች የሰላም ጥሪን ተቀብለው ወደ ቀደመ ህይወታቸው እየተመለሱ መሆኑም ተመላክቷል። በሰሜን ሸዋ ዞንና በደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ለሚገኙ የቀድሞ ታጣቂዎች በደብረ ብርሃን የስልጠና ማዕከል ዛሬ የተሀድሶ ስልጠና መስጠት ተጀምሯል። ከተመላሾቹ መካከል ከምንጃር ሸንኮራ ወረዳ የመጣው ፈለቀ ሰጤ በተሳሳተ መንገድ በመጓዝ በህዝብ ላይ ባደረሰው በደልና ጥፋት መጸጸቱን ተናግሯል። ትግሉ የህዝብን ሃብትና ንብረት በመዝረፍ ለመበልጸግ ያለመ መሆኑን በመገንዘቤ የመንግስትን የሰላም ጥሪ ተቀብዬ ወደሰላም ተመልሻለሁ ብሏል። ስንፈጽመው በነበረው የጥፋት ተግባር ህብረተሰቡን ከመበደል ባለፈ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴው በመስተጓጎሉ ለጸጸት መዳረጉን ገልጾ፣ ከተሀድሶ ስልጠና በኋላ ህዝቡን ለመካስ እንደሚሰራ ተናግሯል። ከባሶና ወራና ወረዳ የመጣው ተስፋዬ ጌታቸው በበኩሉ፥ የህብረተሰቡን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ በማወክ ባደረስኩት በደል በመጸጸትና የመንግስትን ጥሪ በመቀበል ተመልሻለሁ ብለዋል። አሁንም ጫካ ቀርተው በጥፋት ተግባራቸው የቀጠሉት ትምህርት እንዲቋረጥ፣ንጹሀን እንዲገደሉ በማድረግ የሚመለስ የፖለቲካ ጥያቄ እንደሌለ ተገንዝበው ወደሰላማዊ ህይወት እንዲመለሱ ጥሪ አቅርቧል። በቀጣይ በየአካባቢው በሚከናወኑ የሰላምና የልማት ሥራዎች ላይ ጉልህ አስተዋጾ በማድረግ የበደሉትን ህዝብና መንግስት ለመካስ ዝግጁነታቸውንም አረጋግጠዋል። ከቡልጋ ከተማ አስተዳደር የመጣው ሙሉቀን መስፍን በበኩሉ፥ ትግሉ የአማራን ህዝብ ጥያቄ የሚያስመልስ ሳይሆን የጥቂቶች ሀብት ማከማቻ እየሆነ መምጣቱን በመገንዘብ የመንግስትን የሰላም አማራጭ መቀበሉን ተናግሯል። የአማራ ክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ምክትል ሀላፊ አቶ ደጀኔ ልመንህ እንዳሉት፥ ሰላምን በዘላቂነት ለማጽናት ከህዝብ ጋር የተደረጉ ተደጋጋሚ ውይይቶች ውጤት እያስገኙ ናቸው።   በአሁኑ ወቅት በክልሉ በርካታ ታጣቂዎች የሰላምን ጥሪ ተቀብለው ወደ ቀደመ ህይወታቸው እየተመለሱ መሆኑን ጠቁመው፣ ለተመላሾቹ የተሃድሶ ስልጠና በመስጠት በፈለጉት የሙያ ዘርፍ እንዲሰማሩ እየተደረገ መሆኑንም ተናግረዋል። አሁንም በጫካ የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎች በሀይል የሚመለስ ምንም አይነት ጥያቄ እንደማይኖር በመረዳትና የጥፋት ተግባራቸውን በመተው የሰላምን አማራጭ እንዲቀበሉ አስገንዝብዋል። የሰሜን ሸዋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ መካሻ ዓለማየሁ በበኩላቸው፥ በዞኑ የሰፈነው ሰላም ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እንቅስቃሴ እንዲሻሻል መልካም እድል ፈጥሯል ብለዋል። መንግስት ያቀረበውን የሰላም ጥሪ ተቀብለው የተመለሱ ወንድሞች አሁንም ሳይመለሱ በጫካ ያሉ ታጣቂዎችን መክረው ወደሰላም እንዲመለሱና የበደሉትን ህዝብ እንዲክሱ የድርሻቸውን እንዲወጡ አስገንዝበዋል።   በደብረብርሃን ከተማ አስተዳደርና በዙሪያው እየሰፈነ ያለው ሰላም ለኢንዱስትሪና ለንግድ ሥራዎች መስፋፋት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የተናገሩት ደግሞ የከተማ አስተዳደሩ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት ናቸው። ወደሰላም የመጡ የቀድሞ ታጣቂዎችን በቀጣይ በሚፈልጉት የሥራ ዘርፍ ለማሰማራት በአስተዳደሩ በኩል አስፈላጊውን ድጋፍ ይደረጋል ብለዋል።
በክልሉ በሰፈነው ሠላም ልማትን የማጠናከር ሥራ ይቀጥላል
Jan 11, 2026 208
አሶሳ፤ጥር 3/2018 (ኢዜአ)፦በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሰፈነውን ሠላም በመጠቀም ልማትን የማጎልበት ሥራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አሻድሊ ሀሰን ተናገሩ። የቤኒሻንጉል ብሔረሰብ ምክር ቤት ከመንጌ ወረዳ መስተዳድር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት "የህዝብ ለህዝብ ትስስር መድረክ" በመንጌ ወረዳ ተካሂዷል።   በመድረኩ ላይ የተገኙት የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን፤ በክልሉ የህዝቦችን አንድነት በማጠናከር ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን ተናግረዋል። የህዝበ ለህዝብ ትስስር መድረኩ በክልሉ የሰፈነውን ሠላም ለማጽናትና አብሮነትን ለማጠናከር የሚያግዝ ነው ብለዋል። ክልሉ የተፈጥሮ ሀብትን ወደ ልማት በመቀየር የዜጎችን ተጠቃሚነት በተግባር እያረጋገጠ መሆኑን የጠቀሱት ርዕሰ መስተዳድሩ፥ ፍትሃዊ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ በሁሉም የክልሉ አካባቢዎች ህብረተሰቡን ያሳተፈ የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቁመዋል። ህብረተሰቡ በልማት ስራዎች ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ በማጠናከር ለሁለንተናዊ ብልጽግና መረጋገጥ መትጋት ይጠበቅበታል ሲሉም ተናግረዋል።   የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አስካለች አልቦሮ በበኩላቸው፤ የህዝቦችን ትስስር ማጠናከር ለጋራ ዓላማ እንዲቆሙ የሚያደርግ እና የዜጎችን ሁሉን አቀፍ ተሳትፎ የሚያሳድግ ነው ብለዋል። በቀጣይም ተመሳሳይ መድረኮችን በማዘጋጀት ህብረተሰቡ ክልላዊ እና ሀገራዊ የልማት አጀንዳዎች ላይ የጋራ ግንዛቤ እንዲይዝ ይደረጋል ነው ያሉት። የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን ማጠናከር ለዘላቂ ሠላም እና አብሮነት የሚኖረው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው ያሉት ደግሞ በብልጽግና ፓርቲ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኢሳቅ አብዱልቃድር ናቸው።   የመደመር መንግስት ከህብረተሰቡ የሚነሱ የልማት ጥያቄዎችን በማድመጥ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ተናግረው ህብረተሰቡ የልማት ስራዎች ላይ የሚያደርገውን ተሳትፎ አጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል። በመድረኩ ላይ የክልል፣ የዞንና የከተማ አስተዳደር አመራሮች፣ ከክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች የተውጣጡ የህብረተሰብ ክፍሎች እና የመንጌ ወረዳ ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በኢትዮጵያ በመከናወን ላይ ያሉ ስራዎች ለትውልድ ምንዳ ማውረስ የሚያስችሉ ናቸው -ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር)
Jan 10, 2026 158
ባህር ዳር፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት አመታት በሁሉም ዘርፎች የተከናወኑ እና በመከናወን ላይ ያሉ ስራዎች ለትውልድ ምንዳ ማውረስ የሚያስችሉ ናቸው ሲሉ በብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና የአቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር) ተናገሩ። ከሁሉም ክልሎች የተውጣጡ የብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ አመራሮች በተገኙበት የ6 ወራት የዕቅድ አፈፃፀም ግምገማና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ መድረክ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው።   በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና የአቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር)፤ በኢትዮጵያ ባለፉት ጥቂት አመታት በሁሉም ዘርፎች የተከናወኑ እና በመከናወን ላይ ያሉ ስራዎች ለትውልድ ምንዳ ማውረስ የሚያስችሉ ናቸው ብለዋል። ለዚህም ብልጽግና ፓርቲ ትናንትን፣ ከዛሬና ነገ ጋር አሰናስሎና አስተሳስሮ ለትውልድ ምንዳ ለማውረስ የሚያስችሉ ስኬታማ ስራዎችን አከናውኗል ብለዋል። ፓርቲው በተለይም ባለፉት ዓመታት ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና የዲፕሎማሲ ድሎችን ማስመዝገቡን አንስተው ከተረጅነት የመውጣት ጥረትም ስኬት የተመዘገበበት መሆኑን ገልጸዋል። በግብርና ልማት፣ በማዕድን፣ በቱሪዝም፣ በቴክኖሎጂ፣ በኢንዱስትሪ እና ሌሎችም ብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፎች የላቀ ስኬት ተመዝግቧል ብለዋል። በግንቦት ወር የሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ ሰላማዊ፣ ነፃ፣ እና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲከናወን ብልጽግና የድርሻውን ለመወጣት ከወዲሁ ዝግጅት ማድረጉንም ተናግረዋል።   በብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ይርጋ ሲሳይ፤ በክልሉ ተከስቶ የነበረውን የፀጥታ ችግር በመቀልበስ ወደ ዘላቂ ሰላምና የተሟላ ልማት መገባት መቻሉን ገልጸዋል። በክልሉ በተለይም ለሰላም አማራጭ ትኩረት በመስጠት ስኬታማ ስራ መሰራቱን አንስተው የሰላምን አማራጭ በሚገፋ የጥፋት ቡድን ላይም የተጠናከረ ህግ የማስከበር እርምጃ መወሰዱን አንስተዋል። ለሁለት ቀናት የሚካሄደው መድረክ ብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ የስድስት ወራት የዕቅድ አፈፃፀም ተገምግሞ ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ውይይት የሚደረግ መሆኑ ታውቋል።
የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ በሁሉም መስኮች የተጀመሩ የልማት ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተገኘባቸው ነው
Jan 10, 2026 174
ሰመራ፤ ጥር 2/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ በሁሉም መስኮች የተጀመሩ የልማት ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተገኘባቸው መሆኑን የብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ፍቃዱ ተሰማ ተናገሩ። "ጠንካራ አደረጃጀት ለጠንካራ ፓርቲ" በሚል መሪ ሀሳብ በብልፅግና ፓርቲ ዋና ፅህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ የ2018 የ6 ወራት አፈፃፀም ግምገማ እና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ መድረክ በሰመራ ከተማ እየተካሄደ ነው። መድረኩን ያስጀመሩት የብልፅግና ፓርቲ የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ፍቃዱ ተሰማ እንዳሉት ፓርቲው የኢትዮጵያን ብልፅግና የሚያረጋግጡ የተለያዩ የልማት ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል።   እየተከናወኑ በሚገኙ የልማት ስራዎችም የብልፅግና አይቀሬነት እየተረጋገጠ መምጣቱን ጠቅሰው ከዚህ ውስጥ አንዱ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ መሆኑን ተናግረዋል። በበጀት ዓመቱ ግማሽ ዓመትም ሀገርን ወደ ከፍታ ያሸጋገሩ ሌሎች ትላልቅ ፕሮጀክቶች የተፈጸሙበት እና ይፋ የተደረጉበት መሆኑንም ገልጸዋል። ለከተሞች ዕድገት ወሳኝ የሆኑ አንፀባራቂ ስራዎች በተለያዩ ከተሞች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተው ይኼም ከተጠቃሚነት አኳያ የህብረተሰብን ጥያቄዎች መመለስ የሚያስችሉ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአጠቃላይ የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ በሁሉም መስኮች የተጀመሩ የልማት ስራዎች ተጨባጭ ውጤት እየተገኘባቸው መሆኑን ነው ያብራሩት። በብልፅግና ፓርቲ የአፋር ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊ መሐመድ ሁሴን በበኩላቸው ፓርቲው ባለፉት ዓመታት ሁሉንም አኩል ተሳታፊ እና ተጠቃሚ ያደረገ መሆኑን አንስተዋል።   በክልሉም ከዚህ በፊት ያልተለመዱ ሰፋፊ የግብርና ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰው በሰመራ ከተማም የተከናወነው የኮሪደር ልማት ስራ ከተማዋን ለነዋሪው ጽዱ እና ምቹ ማድረግ አስችሏል ብለዋል።   በክልሉ በተለይም ከተረጂነት ወደ ምርታማነት በሚደረገው ጉዞ ተስፋ ሰጪ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በብልፅግና ፓርቲ የአፋር ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ ወልኦ አይትሌ ናቸው።
አዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት ነዋሪዎች መንግስታዊ አገልግሎቶችን በቅርበት እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታ ፈጥሯል
Jan 9, 2026 414
ሮቤ ፤ጥር 1/2018 (ኢዜአ):-በኦሮሚያ ክልል ተግባራዊ የተደረገው አዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት መንግስታዊ አገልግሎቶችን በቅርበት እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን በባሌ ዞን የሀረና ቡሉቅ ወረዳ ነዋሪዎች ገለጹ። የዞኑ አስተዳደር በበኩሉ በ189 ቀበሌዎች የተዋቀረው አደረጃጀት ለነዋሪዎች አገልግሎት በቅርበት ለመስጠት ከማስቻሉ ባለፈ ጊዜና ወጪን በመቆጠብ በልማት ሥራዎች ላይ እንዲያተኩሩ ማድረጉን ገልጿል። አዲሱን የቀበሌ አደረጃጀት በማስመልከት አስተያየታቸውን ከሰጡ የሀረና ቡሉቅ የቁምቢ ቀበሌ ነዋሪዎች መካከል አቶ ሀሰን አህመድ እንዳሉት፣ አደረጃጀቱ ምቹና ቀልጣፋ አገልግሎቶች በቅርበት ለማግኘት አስችሏቸዋል። ከዚህ በፊት መንግስታዊ አገልግሎቶችን ለማግኘት ወደ ወረዳና ከተማ አስተዳደር የሚያደርጉት ምልልስ ጊዜና ድካም እንደነበረው አስታውሰው "አዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት ይህንን በማቃለል ተጠቃሚ አድርጎናል" ብለዋል።   ሌላኛው ተገልጋይ አቶ አህመድ መሐመድ በበኩላቸው እንዳሉት የቀበሌ አደረጃጀቱ የህዝብን የልማት ተሳትፎ በማሳደግ ከዚህ በፊት የነበሩት የመሰረተ ልማት ችግሮች በህብረተሰቡ ተሳትፎ እንዲፈቱ ዕድል ፈጥሯል። በአጭር ጊዜ ውስጥ ህብረተሰቡን በማሳተፍ ከተከናወኑ የልማት ሥራዎች መካከል ድልድይና ተጨማሪ የመማሪያ ክፍሎችን ለአብነት ጠቅሰዋል። የሀረና ቡሉቅ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ኢብራሂም ሀሰን በበኩላቸው አዲሱ አደረጃጀት የወረዳውን ህዝብ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በቅርበት ለመመለስ እያገዘ መሆኑን ተናግረዋል። የባሌ ዞን አስተዳዳሪ ተወካይ አቶ ብርሃኑ አርፋሳ በበኩላቸው በዞኑ የሚገኙ 189 ቀበሌዎች በአዲሱ አደረጃጀት ተዋቅረው ወደ ሥራ መግባታቸውን ተናግሯል። በቀበሌ አደረጃጀቶችም አመራሮች ተመድበው ህብረተሰቡን በቅርበት እንዲያገለግሉ መደረጉን ገልጸዋል። እንደ አቶ ብርሀኑ ገለጻ በአዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት እየተሰጠ ያለው የህዝብ አገልግሎት ከዚህ በፊት ወደ ዞንና ወረዳዎች በተደጋጋሚ ይመጡ የነበሩ ቅሬታዎችን እየቀነሰና የህዝብ እርካታን እየጨመረ መጥቷል። በቀበሌዎቹ የተመደቡ አመራሮችና በለሙያዎች ህብረተሰቡን በተሻለ እንዲያገለግሉ የአቅም ግንባታ ሥልጠናና የድጋፍና ክትትል ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በኦሮሚያ ክልል የአገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻልና የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በቅርበት ለመፍታት አዲስ የቀበሌ አደረጃጀት ተግባራዊ መደረጉ ይታወሳል። አደረጃጀቱ ህዝቡ በልማት ተጠቃሚ እንዲሆንና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎቹም በህዝብ ተሳትፎ መፍትሄ እንዲያገኙ ያለመ መሆኑ እንዲሁ።  
ኢትዮጵያ እና ቻይና በዘርፈ-ብዙ ጉዳዮች ላይ ግንኙነታቸውን በይበልጥ ለማጠናከር ተወያዩ
Jan 8, 2026 270
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 30/2018 (ኢዜአ)፡- ኢትዮጵያ እና ቻይና በተለያዩ በርካታ ጉዳዮች ላይ ግንኙነታቸውን በይበልጥ አጠናክረው ማስቀጠል በሚችሉበት ሁኔታ ላይ መወያየታቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ።   ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ (ዶ/ር) በማኅበራዊ ትሥሥር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት፤ ዛሬ የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ይን ተቀብዬ በጽናት በሚጓዘው የኢትዮጵያ እና ቻይና የመንግሥት እና ሕዝብ ግንኙነት ላይ ተነጋግረናል ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የቻይና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዋንግ ይን በብሔራዊ ቤተመንግሥት ተቀበሉ   ኢትዮጵያ እና ቻይና ለአስርት ዓመታት የዘለቀ ጠንካራ ግንኙነት እንዳላቸውም ገልጸዋል። ይኽ ግንኙነት በቅርቡ ወደ በሁኔታዎች የማይለዋወጥ የስትራቴጂክ ትብብር ማደጉንም አስታውቀዋል።   በተለያዩ የልማት ትብብር ርዕሰ ጉዳዮችን ለማከናወን ያለንን ጽኑ አቋም በማስቀጠል ላይ ውይይት አድርገናልም ነው ያሉት።   በኢኮኖሚ፣ ንግድ፣ መሠረተ ልማት፣ የኃይል አቅርቦት እና ትራንስፖርት ብሎም አዲስ በመፈጠር ላይ ባሉ እንደኢ-ኮሜርስ፣ ዲጂታል ኢኮኖሚ፣ ሰው ሠራሽ አስተውሎት እና አረንጓዴ ኃይል ልማት ላይ ትብብራችንን ለማጠናከር ተወያይተናል ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።  
የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባካሄደው 51ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ
Jan 6, 2026 424
አዲስ አበባ፤ታኅሣስ 28/2018 (ኢዜአ)፦ የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 51ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል። በዚህም መሰረት፦ 1. በቅድሚያ ምክር ቤቱ የተወያየው የማዳበሪያ ምርት ፈቃድ እና የፖታሽ ማዕድን ምርት ፈቃድ ረቂቅ ስምምነቶች ላይ ነው፡፡ ለምክር ቤቱ የቀረቡት ሁለት ረቂቅ ስምምነቶች የውጭ ምንዛሪ ግኝትን ለማሳደግ፣ ለዜጎች የስራ ዕድል ለመፍጠር፣ ሀገራችን ለማዳበሪያ ግዥ የምታወጣውን ከፍተኛ የውጪ ምንዛሪ ለማስቀረት እና ለሀገራችን አርሶ አደሮች ወቅቱን የጠበቀ የማዳበሪያ ስርጭት እንዲኖር ለማድረግ ትልቅ ጠቀሜታ ያላቸውና ከአካባቢ ጥበቃና ከማህበረሰብ ተጠቃሚነት አንጻርም የመንግስትን የፖሊሲ አቅጣጫ የተከተሉ መሆናቸውን በማረጋገጥ የማዕድን ሚኒስቴር ስምምነቶቹን እንዲፈራረምና ወደ ስራ እንዲገቡ ምክርቤቱ በሙሉ ድምጽ ይሁንታ ሰጥቷል፡፡   2. በመቀጠል የቤት ልማት ረቂቅ ፖሊሲ ምከር ቤቱ የተወያየበት ሌላው አጀንዳ ነው፡፡ ባለፉት አመታት በቂ የቤት አቅርቦት እንዲኖር የተደረጉ ጥረቶች ቢኖሩም አሁንም የቤት አቅርቦትና ፍላጎት የተጣጣመ አይደለም፡፡ በመሆኑም በከተማና በገጠርለሚኖሩ ለሁሉም ዜጎች አቅምን ያገናዘበ፣ ተደራሽ እና በቂ የመኖሪያ ቤት አቅርቦት በዘላቂነት ማረጋገጥ የሚያስችል የፖሊሲና የህግ ማዕቀፍ መዘርጋት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ፖሊሲው ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ምክር ቤቱም በፖሊሲው ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ግብአቶችን በማከል በምክር ቤቱ ከጸደቀበት ቀን ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረግ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 3. ከዚያም ምክር ቤቱ የተወያየው ከኮሪያ ኤክስፖርት-ኢምፖርት ባንክ ጋር በተደረገው የፋይናንስ ድጋፍ ስምምነት ላይ ነው፡፡ የብድር ስምምነቱ ለህከምና መሳሪያዎች አቅርቦት ፕሮጄክት ምዕራፍ 2 ማስፈፀሚያ የሚውል 30,000,000 /ሰላሳ ሚሊዮን/የአሜሪካን ዶላር የሚያስገኝ ሲሆን የሀከምና መሳሪያዎችን ችግር የሚፈታ፣ ዝቅተኛ ወለድ 0.01% የሚከፈልበት እና የከ5 አመት የችሮታ ጊዜን ጨምሮ በ40 ዓመት ተከፍሎ የሚጠናቀቅ ነው፡፡ ምከር ቤቱም ብድሩ ከሀገራችን የብድር አስተዳደር ፖሊሲ ጋርየሚጣጣም መሆኑን በማረጋገጥ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምከር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡   4. ሌላው ምክር ቤቱ የተወያየው የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት ለሚሰጣቸው የተለያዩ አገልግሎቶች የሚከፈል የአገልግሎት ከፍያን ለመወሰን የወጣ ደንብ ላይ ነው፡፡ ተቋሙ ለተገልጋዮች ጥራትና ተዓማኒነት ያላቸው አገልግሎቶች ለመስጠት የሚያወጣቸውን ቀጥተኛና ቀጥተኛ ያልሆኑ ወጪዎች የአገልግሎቱ ቀጥተኛ ተጠቃሚ ከሆነው የህብረተሰብ ክፍል ተመጣጣኝ ከፍያ በማስከፈል እንዲሸፍን ለማድረግ እንዲያስችለው ረቂቅ ደንቡ ተዘጋጅቶ ለምከር ቤቱ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በጉዳዩ ላይበሰፊው ከተወያየበት በኋላ ደንቡ በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ላይ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረግ በሙሉ ደምጽ ወስኗል፡፡ 5. እንዲሁም የኅብረት ሥራ ማህበራት ማሻሻያ አዋጅ ምክር ቤቱ የተወያየበት ሌላው አጀንዳ ነው፡፡ በስራ ላይ ያለው የኅብረት ሥራ ማህበራት አዋጅ ቁጥር 985/2009 ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ከተቀመጡ አቅጣጫዎች ጋር የተጣጣመ እንዲሆን ለማድረግ አዋጁን ማሻሻል አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ማሻሻያ አዋጁ ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በማሻሻያ አዋጁ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 6. በማስከተልም የኢትዮጵያ የአቪዬሽን ሴኩዩሪቲ አዋጅን ለማሻሻል የወጣ አዋጅ ላይ ምክር ቤቱ ተወያይቷል፡፡በአየር ትራንስፖርት ደህንነት፡ አስተማማኝነትና ቅልጥፍና ላይ የሚስተዋሉ የደህንነት ስጋቶችን በብቃት ለመከላከል የሚያስችል አሰራር ለመተግበርየአቪዬሽን ሴኩዩሪቲ አዋጅ ቁጥር 432/1997ን ማሻሻል አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ማሻሻያ አዋጁ ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በማሻሻያ አዋጁ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 7. በመቀጠል ምክር ቤቱ የተወያየው በሁለት ደንቦች ላይ ነው፡፡ የመጀመሪያው የመሶብ አገልግሎትን ለማቋቋም የወጣው ደንብ ተገልጋዮች የመንግስት አገልግሎት ለማግኘት የሚያባከኑትን ጊዜ፣ ወጭ እና ጉልበት በመቆጠብ የተገልጋይ እርካታን የሚጨምርየአንድ ማእከል አገልግሎት አሰጣጥ ለመተግበር እንዲያስችል የቀረበ ሲሆን ሁለተኛው የኢትዮጵያ የብቃትና ሥራ አመራርኢንስቲትዩት አደረጃጀት፣ ሥልጣን እና ተግባር ለመወሰን የወጣው ደንብ ተቋሙ በአዋጅ የተሰጠውን ተግባርና ሃላፊነት ለመወጣት እንዲያስችለው ተዘጋጅቶ የቀረበ ነው፡፡ምክር ቤቱም በሁለቱም ደንቦች ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ታትመው ከወጡበት ቀን ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረጉ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡   8. ከዚያም ምክር ቤቱ የተወያየው የሁሉን አቀፍ የተደራሽነት ፈንድ የገቢ መጠን፣ ምንጭ እና አስተዳደርን ለመወሰን የወጣ ደንብ ላይ ነው፡፡ ደንቡ በኢትዮጵያ የኮሙኒኬሽን አገልግሎት አዋጅ ቁጥር 148/2011 አንቀጽ 49 ንዑስ አንቀጽ (3) መሰረት የተቋቋመው የኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሁሉን አቀፍ ተደራሽነት ፈንድ የገቢ መጠንና ምንጭ እንዲሁም ፈንዱ ስለሚተዳደርበት ሁኔታ ለመወሰን ተዘጋጅቶ የቀረበ ነው፡፡ ምክር ቤቱም በደንቡ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ በፌዴራል ነጋሪት ጋዜጣ ታትሞ ከወጣበት ቀን ጀምሮ ተግባራዊ እንዲደረግ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ 9. በመቀጠል ምክር ቤቱ የተወያየው በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲዊ ሪፐብሊክ የስፖርት ፖሊሲ ላይ ነው፡፡ በስራ ላይ ያለው የስፖርት ፖሊሲ የማህበረሰቡን የስፖርት ተሳትፎ ከማረጋገጥ፣ በቴክኖሎጂ የተደገፈ የመረጃ ስርአት ከመዘርጋት፣ ንጹህ ስፖርትን ለማስፋፋት የአበረታች ቅመሞችና ዘዴዎች ከመከላከል እና ስፖርትን ለማህበራዊ ልማት ከመጠቀም አንጻር ከፍተቶች የነበሩበት በመሆኑ ፖሊሲውን ለማሻሻል ረቂቁ ተዘጋጅቶ ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በፖሊሲው ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ግብአቶችን በማከል ከጸደቀበት ቀን ጀምሮ በስራ ላይ እንዲውል በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡   10. በመጨረሻም ምክር ቤቱ የተወያየው የፌዴራል ስፖርት ልማት እና አስተዳደር ረቂቅ አዋጅ ላይ ነው፡፡ የስፖርት ዘርፍ ካለው ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ፋይዳ እንዲሁም አስተዳደራዊ ውስብስብነት አንጻር ዘርፉን በአግባቡ ለመምራት ዘመናዊ፣ አሳታፊና አካታች የሆነ የህግ ማዕቀፍና አስተዳደራዊ የአሰራር ሥርዓት መዘርጋት የሚያስችል ረቂቅ አዋጅ ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በረቂቅ አዋጁ ላይ በሰፊው ከተወያየ በኋላ ግብአቶችን በማከል ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡  
ሀገራዊ ምክክር፣ የዲሞክራሲ ባህልና የተቋማት ግንባታ ለሁሉም የምትመች ሀገር ለመገንባት ወሳኝ ናቸው
Jan 6, 2026 221
አዲስ አበባ፤ ታኅሣስ 28/2018(ኢዜአ)፡- ሀገራዊ ምክክር፣ የዲሞክራሲ ባህልና የተቋማት ግንባታ ሥራዎች ለሁሉም የምትመች ሀገር ለመገንባት ወሳኝ መሰረት መሆናቸውን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያን ችግሮች በመፍታት በተደመረ አቅም ሀገርን ለማበልፀግ ምሁራን ሀሳብ ከማመንጨትና ችግር ፈች ጥናት ከማድረግ ጀምሮ በተግባር ለውጥ የሚያመጣ ሥራን ሊከውኑ እንደሚገባም ተናግረዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ 75ኛ ዓመት የምሥረታ በዓልን በማስመልከት “የምሁራን ሚና ለሀገር ብልፅግና” በሚል መሪ ሀሳብ በተዘጋጀ የውይይት መድረክ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ማብራሪያ ሰጥተዋል። የፖለቲካ ልዩነቶችን እንዴት ነው መፍታት የሚቻለው በሚል ለተነሳላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፥ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የፖለቲካ ልዩነቶችን መፍታት የቁርጠኝነትና የአቋም ጉዳይ መሆን አለበት ብለዋል። በየአካባቢው ያሉ የጽንፍ እሳቤዎች ኢትዮጵያን አንድ እርምጃ ወደ ፊት እንደማይወስዱ በማንሳት፥ ኢትዮጵያ የጋራችን ናት በሚል እሳቤ አምነን ከሠራን ወደተሻለ ምዕራፍ እንሻገራለን ነው ያሉት። ታሪክን በሚዛን፣ ዛሬን በትጋት፣ ነገን በተስፋ ነው የምንመለከተው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ ለሁሉም ህብረተሰብ እኩል እድል መስጠት እንደሚገባ ጠቅሰዋል። ጠንካራ ሀገራዊ አንድነት መፍጠር የሚቻለው የወል ትርክት በመገንባት ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ መንግሥት ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ መሆኑን አንስተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም