ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
ከኢትዮጵያ ጋር ያለንን የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር እንሰራለን -አምባሳደሮች
Jan 15, 2026 54
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018 (ኢዜአ)፡ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር እንደሚሰሩ በኢትዮጵያ አዲስ የተሾሙ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች ገለጹ። ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀሥላሴ በኢትዮጵያ አዲስ የተሾሙ የ 14 ሀገራት አምባሳደሮችን የሹመት ደብዳቤ ተቀብለዋል። የሹመት ደብዳቤያቸውን ለፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ ያቀረቡትም የኪርጊስታን፣ ጣልያን፣ ሞሪሺየስ፣ ዛምቢያ፣ጀርመን፣ ጆርዳን፣ ኒውዝላንድ፣ ደቡብ ሱዳን፣ ቡሩኪና ፋሶ፣ ሞዛምቢክ፣ ኬንያ፣ቤላሩስ፣ ፊሊፒንስ፣ ላቲቪያ ሀገራት አምባሳደሮች ናቸው። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው በሰጡት ማብራሪያ የሹመት ደብዳቤያቸውን ካቀረቡ ሀገራት መካከል 11ዱ ተቀማጭነታቸው በአዲስ አበባ መሆኑን ገልጸዋል። አምባሳደሮቹ ከፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ ጋር ከፍተኛ ውጤት እየተመዘገበበት ባለው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እንዲሁም በንግድ እና ኢንቨስትመንት በሚሰማሩባቸው መስኮች ላይ መወያየታቸውን ገልጸዋል። በተጨማሪም የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅሞች በሚያስከብሩ ስራዎች ዙሪያ ምክክር ማድረጋቸውን ነው የተናገሩት። በውይይቱ አምባሳደሮቹ በኢትዮጵያ እየተመዘገበ ላለው ለውጥ አድናቆት መስጠታቸውን ጠቁመው፥ ሀገሮቻቸው ከኢትዮጵያ ልምድና ተሞክሮ መውሰድ እንደሚፈልጉ መናገራቸውን አንስተዋል። በኢትዮጵያና በሀገራቱ መካከል የሁለትዮሽ ግንኙነትን ለማጠናከር እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል ነው ያሉት። በኢትዮጵያ አዲስ የተሾሙት የጣልያን አምባሳደር ሴም ፋብሪዚ በትምህርት፣ በክህሎት፣ በሳይንሳዊ እና በባህል ትብብር ዙሪያ እንደሚሰሩ ገልጸዋል። በሚኖራቸው ቆይታ ጣልያን ለኢትዮጵያ ጠንካራ ወዳጅ መሆን የምትችልባቸውን መንገዶች ለማየት እንደሚጥሩ ጠቁመዋል። አዲስ የተሾሙት የዛምቢያ አምባሳደር አልበርት ሙቻንጋ በበኩላቸው በግብርና ማለትም በተሻሻሉ የሰብል ዝሪያዎች ላይ ልምድ በመለዋወጥ እና በስፋት በመተግበር ምርታማነትን ለማሻሻል እንደሚሰሩ ገልፀዋል። የኬንያ አምባሳደር ጋልማ ሙክሄ በኢትዮጵያ እና በኬንያ መካከል ያለውን ታሪካዊ የሁለትዮሽ ግንኙነት ለማጠናከር እና ለማሳደግ እንደሚሰሩ ገልጸዋል። በንግድ፣ በኢንቨስትመንት፣ በመከላከያ እና በሌሎች በርካታ ዘርፎች ላይ ይህን ግንኙነት ለማጠናከር በጋራ እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል። የደቡብ ሱዳን አምባሳደር ባክ ቫለንቲኖ የሁለትዮሽ ግንኙነቱን ለማጠናከር በትኩረት እንደሚሰሩ አረጋግጠዋል። ይህንንም በኢትዮጵያ ከሚገኙ ሌሎች አካላት ጋር በቅርበት እንደሚሰሩ አመላክተዋል:: የፊሊፒንስ አምባሳደር ማሬ ቻርሎቴ በቀጣዩ አመት ሁለቱ ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የጀመሩበትን የምስረታ በአላቸውን እንደሚያከብሩም ተናግረዋል። በሁለቱ አገራት መካከል በፖለቲካ፣በኢኮኖሚ እና በህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ጠንካራ ትብብር ለመፍጠር እንደሚሰራ አመላክተዋል። #Ethiopian_News_Agency #ኢዜአ
ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮችን የሹመት ደብዳቤ ተቀበሉ
Jan 15, 2026 68
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018 (ኢዜአ)፡- ፕሬዚዳንት ታዬ አጽቀ ሥላሴ በኢትዮጵያ አዲስ የተሾሙ የ14 ሀገራት አምባሳደሮችን የሹመት ደብዳቤ ተቀብለዋል። የሹመት ደብዳቤያቸውን ለፕሬዚዳንት ታዬ ያቀረቡት፤ የደቡብ ሱዳን፣ ጣልያን፣ ሞሪሺየስ፣ ዛምቢያ፣ ጀርመን፣ ጆርዳን፣ ኒውዝላንድ፣ ቡርኪና ፋሶ፣ ሞዛምቢክ፣ ኬንያ፣ ቤላሩስ፣ ፊሊፒንስ፣ ኪርጊስታን እና የላቲቪያ አምባሳደሮች ናቸው። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ነብያት ጌታቸው በሰጡት ማብራሪያም፤ የሹመት ደብዳቤያቸውን ካቀረቡ ሀገራት መካከል 11ዱ ተቀማጭነታቸው በአዲስ አበባ መሆኑን አስታውቀዋል። ከፍተኛ ውጤት እየተመዘገበበት ባለው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እንዲሁም ሀገሮቻቸው በንግድ እና ኢንቨስትመንት በሚሰማሩባቸው መስኮች ላይ አምባሳደሮቹ ከፕሬዚዳንት ታዬ ጋር መወያየታቸውንም ገልጸዋል። በተጨማሪም የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅሞች በሚያስከብሩ ሥራዎች ዙሪያ ምክክር ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል። በውይይቱ አምባሳደሮቹ በኢትዮጵያ እየተመዘገበ ያለውን ለውጥ ማድነቃቸውንም አንስተዋል። በኢትዮጵያና በሀገራቱ መካከል የሁለትዮሽ ግንኙነትን ለማጠናከር እንደሚሠሩም አረጋግጠዋል ነው ያሉት።
የአውሮፓ ሕብረት እና አባል አገሮቹ የኢትዮጵያ አስተማማኝ አጋሮች ናቸው - ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር)
Jan 15, 2026 62
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦የአውሮፓ ሕብረትና አባል አገሮቹ የኢትዮጵያ አስተማማኝ አጋሮች መሆናቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በአውሮፓ የውጭ ጉዳይ አገልግሎት የፖለቲካ ጉዳዮች ምክትል ዋና ፀሐፊ ኡሎፍ ስኩጊን በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል። ኢትዮጵያ እና የአውሮፓ ህብረት የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብራቸውን ለማጠናከር የጋራ ቁርጠኝነታቸውን ገለጹ በውይይታቸውም የአውሮፓ ሕብረትና አባል አገሮቹ የኢትዮጵያ አስተማማኝ አጋሮች መሆናቸውን የገለጹት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ግንኙነቱ በጋራ ዕሴቶች እና ተስፋዎች ላይ የተመሰረተ ወሳኝ አጋርነት መሆኑንም አንስተዋል። ኢትዮጵያ ለቀጣናዊ ውህደት የምታደርገውን ጥረት ያነሱት ሚኒስትሩ እንቅስቃሴው ከአውሮፓ ህብረት ግሎባል ጌትዌይ ኢኒሼቲቭ(Global Gateway initiative) ጋር የሚጣጣም መሆኑን ገልጸው በቀጣናው ውስጥ ኢኮኖሚያዊ ውህደትን ለማሳደግ ያላትን ቁርጠኝነትም ተናግረዋል። እየተከናወነ ያለው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በፈጠረው ምቹ የኢንቨስትመንት ዕድል የአውሮፓ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ የበለጠ የኢንቨስትመንት ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል። ኡሎፍ ስኩጊን በበኩላቸው ህብረቱ ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያዎች የሚያደርገውን ድጋፍና ስትራቴጂያዊ አጋርነት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡ ኢትዮጵያ የኮፕ 32 አስተናጋጅ ሆና በመመረጧ የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን የኢትዮጵያን የልማት ውጥኖች ከግብ ለማድረስ ህብረቱ አስፈላጊውን ትብብር ያደርጋል ብለዋል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ እደሚያመለክተው በውይይታቸው ሁለቱም ወገኖች በጋራ ጥቅም ላይ በሚያተኩሩ ጉዳዮች አብረው ለመስራት ተስማምተዋል።
የክልሉን የልማት አቅም ወደ ተጨባጭ ውጤት ለመቀየር ሰላምን ማጽናት ቀዳሚ ተግባር ነው
Jan 15, 2026 55
አዲስ አበባ፤ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ያለውን ሰፊ የልማት አቅም ወደ ተጨባጭ ውጤት ለመቀየር በሁሉም አካባቢዎች ሰላምን ማጽናት ቀዳሚ ተግባር በማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ እሸቱ የሱፍ (ዶ/ር) ገለፁ። በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በአማራ ክልል ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ትብብር የተዘጋጀው የፓናል ውይይት "ሰላምን ማጽናት፤ፀጋን ለማልማት"በሚል መሪ ሃሳብ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። የአማራ ክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ እሸቱ የሱፍ (ዶ/ር) በክልሉ የተከናወኑ "የሰላምና ፀጥታ ስራዎችና እምርታዎች" በሚል ርዕስ የመወያያ ጽሁፍ አቅርበዋል። በጽሁፋቸው በክልሉ ሰላምን ለማጽናት የተከናወኑ ተግባራት ተጨባጭ ውጤት እያመጡ መሆኑን ጠቅሰው፤ የተገኙ የሰላም እመርታዎችን ጠብቆ ማስቀጠል ለልማት ስራዎች መሳካት ወሳኝ መሆኑን ገልፀዋል። የህዝቡን ደህንነት በዘላቂነት ለማረጋገጥ የተከናወኑ ስራዎች በክልሉ ልማትን ለማፋጠን ወሳኝ በመሆናቸው ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በክልሉ የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ ህብረተሰቡ ከመንግሥት ጎን በመሰለፍ ያበረከተው አስተዋፅኦ ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል። ክልሉ ያለውን ሰፊ የልማት አቅም ወደ ተጨባጭ ውጤት ለመቀየር በሁሉም አካባቢዎች ሰላምን ማጽናት ቀዳሚ ተግባር በማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል። የአማራ ክልል ኢንዱስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ አቶ እንድሪስ አብዱ በበኩላቸው፤ "የክልሉ ፀጋዎችና የኢንቨስትመንት አማራጮች” በሚል ርዕስ የመነሻ ጽሁፍ አቅርበዋል። በጽሁፋቸውም ክልሉ ለኢንቨስትመንት ምቹ የሆኑና ያልተነኩ በርካታ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ፀጋዎች ባለቤት መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ ለማዕድን፣ ለቱሪዝም፣ ለእንስሳት ሀብት ልማት፣ ለውሃ እና ለመሬት ልማት ምቹ የሆኑ በርካታ ዕድሎች መኖራቸውን አብራርተዋል። የክልሉ የሥነ-ምህዳር አወቃቀርና ምቹ የአየር ንብረት ለግብርና ዘርፍ ዕድገት እምቅ አቅም እንዳለው ጠቁመዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ በቅርስነት የተመዘገቡ ታሪካዊ ቦታዎች፣ ተፈጥሯዊ መስህቦች እና የማይዳሰሱ ሃይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶች የክልሉ የቱሪዝም ሀብት መገለጫ ናቸው ብለዋል። እነዚህን ሀብቶች በተገቢው መንገድ በማልማት የቱሪዝም ዘርፉን የኢኮኖሚ ምሰሶ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ አመላክተዋል። በክልሉ የሚገኙ የከበሩ ማዕድናት፣ የኮንስትራክሽን ግብዓቶች እና ለኢንዱስትሪ ልማት አመቺ ሁኔታዎች ለኢንቨስትመንት መዳረሻ መሆናቸውን ጠቅሰዋል። እነዚህን የተፈጥሮ ፀጋዎችና የኢንቨስትመንት አማራጮች በአግባቡ በመጠቀም የክልሉን አልፎም የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ማሳደግ ይቻላል ብለዋል፡፡ በዚህ ረገድ የግል ባለሀብቶች ሚና ከፍተኛ መሆኑን በማንሳት የክልሉ መንግስት ለባለሀብቶች አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የአማራ ክልል ፕላንና ልማት ቢሮ ኃላፊ ደመቀ ቦሩ (ዶ/ር) በበኩላቸው "የአማራ ክልል የልማት ተስፋዎችና የህዝብ ተጠቃሚነት" በሚል ርዕስ ባቀረቡት ጽሁፍ ክልሉ የረጅም፣ የመካከለኛ እና የአጭር ዘመን እቅድ አዘጋጅቶ ወደ ተግባር መግባቱን ተናግረዋል። በዚህም በ2027 የአማራ ክልል በመሠረታዊ ኢንዱስትሪ ምርቶች የራሱን ፍላጎት የሸፈነ እና የተሳካ የመዋቅራዊ ሽግግር በማድረግ የክልሉን ሁለንተናዊ እድገት ለማረጋገጥ በማቀድ እየተሰራ ነው ብለዋል። በ2042 ክልሉ በዓለም አቀፍ ደረጃ በቴክኖሎጂ ተወዳዳሪ የሆነ የዘመናዊ ኢኮኖሚ ባለቤት እና የበለጸገ ማሕበረሰብ ሆኖ ማየት የዕቅዱ አካል መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ የክልሉን ሠላምና ደህንነት እንዲሁም የህግ የበላይነት ማረጋገጥ፤ የተቋማትን የመፈፀምና የማስፈፀም አቅም መገንባት ስትራቴጂክ ጉዳይ ነው ብለዋል። ክልላዊ ወጎችን፣ ዕሴቶችን እና ባህሎችን በማዳበር በሥነ-ምግባር የታነፀ ትውልድ ማፍራትንም እንዲሁ። በተጨማሪ ሣይንሳዊ ዕውቀትን የማሕበረሰብ እሴት እና የኢኮኖሚ ዕድገት መሠረት ማድረግ፤ ምርታማነትንና ቅልጥፍናን በማሳደግ ጥራት ያለው ኢኮኖሚ መገንባት ላይ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የብልጽግና ፓርቲ እቅድ እና እሳቤዎች ተጨባጭ ውጤት እየተገኘባቸው ነው- አቶ አደም ፋራህ
Jan 15, 2026 72
ሆሳዕና፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦የብልጽግና ፓርቲ እቅድ እና እሳቤዎች በሁሉም አካባቢዎች እየተተገበሩ ተጨባጭ ውጤት እየተገኘባቸው መሆኑን የፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንትና በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርአት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ አቶ አደም ፋራህ ገለጹ። የፓርቲው የ2018 በጀት ዓመት የስድስት ወራት ሥራ አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በሆሳዕና ከተማ እየተካሄደ ሲሆን የፓርቲው ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች ሪፖርት ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። አቶ አደም ፋራህ በዚሁ ወቅት ከክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች የቀረበው የፓርቲው ሥራ አፈፃፀም የሚያመለክተው የብልጽግና ፓርቲ እቅድ እና እሳቤዎች በሁሉም አካባቢዎች የህዝብ ቅቡልነት በማግኘት እየተተገበሩ ናቸው ብለዋል፡፡ ክልሎች እና ከተማ አስተዳደሮች ለፓርቲው ስራዎች ውጤታማነት የሚረዳ የተናበበ እቅድ የማዘጋጀት እንዲሁም የፓርቲውን እሳቤ በመረዳት በስነ ምግባር የሚፈፅም ጠንካራ አመራር ለማብቃት በተሰራው ስራ መሻሻሎች መታየታቸውንም ገልጸዋል። በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድም ከህዝቡ ዘንድ የሚነሱ የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመፍታት የመሶብ አንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነትን በማስፋት ውጤት እየተገኘ መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የኮሪደር ልማት ስራ እና የሌማት ትሩፋትን ጨምሮ ሌሎች የፓርቲውን እሳቤዎች በመተግበር ህዝቡ ተባባሪ ሆኖ በመስራቱ ተጨባጭ ውጤቶች ተገኝተዋል ብለዋል። በሁሉም አካባቢዎች ልማትን የማፋጠን እና መልካም አስተዳደር የማስፈን ስራዎች አሁንም በተጠናከረ መልኩ እንደሚቀጥሉ ገልጸው የህዝቡን ፍትሀዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በፓርቲው የተያዙ ሁሉን አቀፍ የእድገትና ትራንፎርሜሽን አጀንዳዎችን ለማሳካት አመራሩ በትኩረት መስራት እንዳለበትም አስገንዝበዋል፡፡ በመድረኩ ላይ የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች፣ የክልሎችና የሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች የብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊዎችና የወጣት ክንፍ አመራሮች እየተሳተፉ ነው፡፡
ሀገራዊ ምክክር ለጠንካራ ሀገር መንግስት ግንባታ መሠረት ነው
Jan 15, 2026 85
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ምክክር ለዘላቂ ሰላም መስፈንና ለጠንካራ ሀገር መንግስት ግንባታ መሠረት መሆኑን በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አዝመራው አንደሞ ገለፁ። በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ትብብር “ሰላምን ማጽናት፤ ፀጋን ለማልማት” በሚል መሪ ሃሳብ የተዘጋጀ የፓናል ውይይት በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አዝመራው አንደሞ “ሀገራዊ ምክክር እና የሰላም ግንባታ” በሚል ርዕስ የመወያያ ጽሁፍ አቅርበዋል። በጹሁፋቸውም በኢትዮጵያ ልዩነቶችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታትና ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የሀገራዊ ምክክር ሚና ከፍተኛ መሆኑን ገልጸዋል። ሀገራዊ ምክክሩ ቅቡልነት ያለው ጠንካራ ሥርዓተ-መንግስት ለመገንባት፣ የማያግባቡ ጉዳዮች ላይ በመመካከር ለመግባባትና የዲሞክራሲ ሥርዓትን ለማፅናት ወሳኝ ነው ብለዋል። ለዚህም የተቋቋመው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የችግሩን ጥልቀትና ባህሪ በመገንዘብ ከሌሎች ሀገራት በተሻለ መንገድና ሥነ ዘዴ ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ጠንካራ ተቋማትን በመገንባት፣ ማህበራዊ ትስስርን በማጠናከርና አዲስ ማህበራዊ ውልን በመፍጠር ልዩነቶችን ወደ ትብብር መቀየር ለዘላቂ ሰላም አይተኬ ሚና እንዳለውም ተናግረዋል። ሀገራዊ ምክክር ፈጣን መፍትሄ ሳይሆን፤ ረጅም ጊዜ የሚፈልግ ኢንቨስትመንት እንደሆነ ጠቁመው፤ ምክክሩ የሰላም ግንባታ መሣሪያ ብቻ ሳይሆን የሀገር ግንባታ መሠረት መሆኑን አስረድተዋል። ሁሉም ኢትዮጵያውያን ይህን ታሪካዊ ዕድል በመጠቀም የወደፊት እጣ ፈንታቸውን እንዲወስኑና ብሔራዊ መግባባት ለመፍጠር የድርሻቸውን እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል።
ሀገራዊ ምክክሩ ሲንከባለሉ የቆዩ ችግሮችን በመቋጨት ዘላቂ መፍትሄ ለማምጣት ታሪካዊ እድል ነው - የፖለቲካ ፓርቲዎች
Jan 15, 2026 146
ሰመራ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ምክክሩ እየተንከባለሉ የመጡ ችግሮችን በመቋጨት ዘላቂ መፍትሄ ለማምጣት ታሪካዊ እድል በመሆኑ በአግባቡ ልንጠቀምበት ይገባል ሲሉ በአፋር ክልል የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ከዝግጅት እስከ አጀንዳ ማሰባሰብ የምክክር ምእራፍ ድረስ በመዝለቅ ሂደቱን በስኬት ለመቋጨት በመስራት ላይ ይገኛል። በሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ የቆዩ አለመግባባቶችን በጠረጴዛ ዙሪያ በምክክር መፍታት የግድ መሆኑ ይታመናል። በመሆኑም በኢትዮጵያ የቆዩ አለመግባባቶችን በዘላቂነት ለመፍታት አካታችና ሁሉን አቀፍ የምክክር ሂደት ተጀምሮ በስኬት በመከናወን ላይ መሆኑ ይታወቃል። በዚህ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው በአፋር ክልል የሚንቀሳቀሱ የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች ሀገራዊ ምክክሩ እየተንከባለሉ የመጡ ችግሮችን በመቋጨት ዘላቂ መፍትሄ ለማምጣት ታሪካዊ እድል መሆኑን ገልጸዋል። የአፋር ነፃ አውጭ ግንባር ፓርቲ(አነግፓ) ሊቀ መንበር ሀንፈሬ አሊሚራህ፤ ሀገራዊ ምክክሩ ሳይፈቱ ዘመናትን የዘለቁ ሀገራዊ ችግሮችን በዘላቂነት መፍታት የሚያስችል ታሪካዊ እድል መሆኑን ተናግረዋል። ፓርቲያቸው ለሀገራዊ ምክክሩ አጀንዳዎችን ቀደም ብሎ ማስረከቡን አስታውሰው በቀጣይነትም ለስኬታማነቱ የነቃ ተሳትፎ፣ እገዛ እና ትብብር እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። በየትኛውም አካባቢ ትጥቅ ይዘው የሚንቀሳቀሱ አካላትም የጥፋት መንገዱን በመተው ለምክክር ዝግጁ መሆን እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። የአፋር አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ግንባር(አርዱፍ) ምክትል ሊቀ መንበር መሐመድ አወል ወግሪስ በበኩላቸው፤ሀገራዊ ምክክሩ ችግሮችን ለመቋጨትና ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት ሁነኛ መፈትሄ መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም የሀገራችንን ችግሮች ወደ መድረክ በማምጣት ችግሮችን በምክክር ለመፍታት እድሉ በሁላችንም እጅ ላይ ይገኛል ብለዋል። ለሀገራዊ ምክክሩ ሂደት መሳካት የእያንዳንዱ ማህበረሰብ ተሳትፎና ሚና ወሳኝ መሆኑን አንስተው ችግሮቻችንን በራሳችን መንገድ ለመፍታት መዘጋጀት አለብን ብለዋል።
በክልሉ ልዩነቶችን በውይይት በመፍታት ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው
Jan 15, 2026 69
አዲስ አበባ፤ ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል ልዩነቶችን በውይይት በመፍታት ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ሲሉ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እውነቴ አለነ ገለፁ። በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ኮሙኒኬሽን ቢሮ ትብብር የተዘጋጀው የፓናል ውይይት "ሰላምን ማጽናት፤ ፀጋን ለማልማት" በሚል መሪ ሃሳብ በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፣ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እውነቴ አለነ፣ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰይፈ ደርቤ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እውነቴ አለነ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ ሰላም ለማንኛውም ሀገራዊ እድገትና የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ የማይተካ ሚና አለው። እንደ ሀገር አለመግባባቶችን በዘላቂነት ለመፍታት መንግስት የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽንን አቋቁሞ እየሰራ መሆኑን ገልጸው፤ ኮሚሽኑ በአሁኑ ወቅት ሀገራዊ ጠቅላላ ጉባኤውን መጥራት የሚያስችል ወሳኝ ምዕራፍ ላይ እንደሚገኝ ጠቁመዋል። በክልሉ ያሉትን እምቅ የልማት ፀጋዎች በአግባቡ ጥቅም ላይ ለማዋልና የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሰላምና መረጋጋት ቀዳሚው ተግባር ሊሆን እንደሚገባም ተናግረዋል። ልዩነቶችን በጠረጴዛ ዙሪያ በውይይት የመፍታት ባህል እንዲዳብር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት አበረታች መሆናቸውን ገልጸው፤ ይህም ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል። በአሁኑ ወቅት ፍላጎትን በኃይል የማስፈጸም አካሄድ ጊዜው ያለፈበት መሆኑንም ገልጸዋል። ይህ የፓናል ውይይት በክልሉ ዘላቂ ሰላምን በማረጋገጥ የልማት ስራዎች ምቹ በሆነ ሁኔታ ለማካሄድ እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን ያግዛል ብለዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰይፈ ደርቤ በበኩላቸው፤ በአማራ ክልል ሰፊ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የልማት ፀጋዎች እንዳሉ ተናግረው፤ እነዚህን ፀጋዎች በአግባቡ ለመጠቀም ሰላምን ማፅናት ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። ኢዜአ ሀገራዊ መግባባትን ለመፍጠርና ለሰላም ግንባታ የሚረዱ መረጃዎችን ለህዝብ ተደራሽ ለማድረግ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸው፤ ይህ የፓናል ውይይትም የዚሁ አካል ነው ብለዋል። የአማራ ክልል ኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አባይ መንግስቴ ሰላምን በማጽናት ረገድ የሚዲያ ተቋማት እና የኮሙኒኬሽን ዘርፍ ወሳኝ መሆናቸውን ተናግረዋል። ይህ መድረክ በክልሉ ሰላምን አፅንቶ ፀጋን ለማልማት የሚደረገውን ጉዞ ለማፍጠን ወሳኝ መሆኑንም ገልፀዋል።
በአማራ ክልል ሰላምን በማፅናት ልማትን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሠራ ነው - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ
Jan 15, 2026 70
አዲስ አበባ፤ጥር 7/2018(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል ችግሮችን በሰላማዊ ውይይት በመፍታትና ሰላምን በማፅናት ሁሉን አቀፍ ልማትን ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሠራ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ። በኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና በአማራ ክልል ኮሙኒኬሽን ቢሮ ትብብር "ሰላምን ማጽናት፤ ፀጋን ለማልማት" በሚል መሪ ሀሳብ የተዘጋጀው የፓናል ውይይት በባህር ዳር ከተማ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ፣ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ እውነቴ አለነ፣ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ሰይፈ ደርቤ እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። የአማራ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ በዚሁ ወቅት ባደረጉት ንግግር ሰላም የልማትና የዕድገት መሠረት መሆኑን ገልጸዋል። በክልሉ ያሉትን ተፈጥሯዊና ሰው ሰራሽ ፀጋዎች፣ የግብርና፣ ማዕድን፣ ቱሪዝም እና ኢንዱስትሪ እምቅ አቅሞችን በአግባቡ ለማልማትና የሕዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሰላምና መረጋጋት ወሳኝ ነው ብለዋል። መንግሥት ለሰላም ቅድሚያ በመስጠት ችግሮችን በዘላቂነት በውይይት ለመፍታት በርካታ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑንም ተናግረዋል። በዚህም 28 ሺህ የቀድሞ ታጣቂዎች የመንግሥትን የሰላም አማራጭ በመቀበል የተሃድሶ ስልጠና ወስደው ወደ ማህበረሰቡ መቀላቀላቸውን ተናግረዋል። የታጣቂ ቡድን አመራሮች ወደ ሰላማዊ መንገድ መምጣታቸው የፖለቲካ ጥያቄዎችን በኃይል ሳይሆን በውይይትና በዲሞክራሲያዊ መንገድ መፍታት ብቸኛውና አስተማማኙ መንገድ መሆኑን ያረጋገጠ ነው ብለዋል። ከዚህም ባለፈ በክልሉ ያለውን የጸጥታ ችግር በዘላቂነት ለመፍታትና ወደ መደበኛ የልማት ሥራዎች ለመመለስ ትልቅ እገዛ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። በዛሬው ዕለት "ሰላምን ማጽናት፤ ፀጋን ለማልማት" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ያለው መድረክ በክልሉ ሰላምን በማፅናት ልማትን ለማረጋገጥ እየተደረገ ላለው ጥረት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል።
ፌዴራል ፖሊስ የሻዕቢያ መንግሥት በፋኖ ስም የሚነግዱ ሽፍቶችን ለማስታጠቅ በስውር የላከውን ከ56 ሺህ በላይ የተለያዩ የጦር መሣሪያ ጥይቶችን በቁጥጥር ሥር አዋለ
Jan 14, 2026 229
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ የሻዕቢያ መንግሥት በፋኖ ስም የሚነግዱ ሽፍቶችን ለማስታጠቅ በስውር የላከውን ከ56 ሺህ በላይ የተለያዩ የጦር መሣሪያ ጥይቶችን በቁጥጥር ሥር ማዋሉን ገለጸ። የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት የሻዕቢያ መንግሥት ከኢትዮጵያ የውስጥ ባንዳዎች እና ታሪካዊ ጠላቶች ጋር በማበር የሀገራችንን ሰላም ለማደፍረስ በፋኖ ስም የሚነግዱ ሽፍቶችን ለማስታጠቅ በስውር የላከውን ከ56 ሺህ በላይ የተለያዩ የጦር መሣሪያ ጥይቶችን ከሁለት ተጠርጣሪዎች ጋር በወልዲያ የፍተሻ ጣቢያ በቁጥጥር ሥር ማዋሉን ገልጿል። እጅ ከፍንጅ በቁጥጥር ሥር በዋሉት ሁለት ተጠርጣሪዎች ላይ በተደረገው የመጀመሪያ ደረጃ ምርመራ ጥይቶቹ በሻዕቢያ መንግሥት እንደተላኩ እና ጽንፈኛው የህወሓት ቡድን በትግራይ ክልል መቀሌ ላይ ተቀብሎ ወደ አማራ ክልል ሸዋሮቢት በማስገባት በፋኖ ስም ለሚነግዱ ሽፍቶች ለማድረስ ሲንቀሳቀሱ እንደነበር ተረጋግጧል። ለሻዕቢያ መንግሥት ድልድይ ሆኖ እየሠራ ያለው ፅንፈኛው የህወሃት ቡድን በፋኖ ስም የሚነግዱ ሽፍቶችን በማስታጠቅ የሀገራችንን ሰላም ለማደፍረስ አቅዶ ከኤርትራ በመቀሌ በኩል በስውር የላከውን 41 ሺህ 999 የክላሽ ጥይት፣ 14ሺህ የብሬን ጥይት እና 800 የድሽቃ ጥይት በአጠቃላይ 56 ሺህ 799 ጥይቶችን ወደ ሸዋሮቢት ለማስገባት ሲያጓጉዙ በወልዲያ የፍተሻ ጣቢያ ተይዘዋል። በሰሌዳ ቁጥር ኮድ 3 አ.አ B94744 የጭነት አይሱዙ ተሽከርካሪ ከሲሚንቶና ከብሎኬት ጋር አመሳስሎ በመጫን በአማራ ክልል ወልዲያ ከተማ አድርገው ሲያጓጉዙ በወልዲያ የፍተሻ ጣቢያ ላይ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት ባደረገው ጠንካራ ክትትልና ፍተሻ እንደተያዙ ፌዴራል ፖሊስ አስታውቋል። ጥር 5 ቀን 2018 ዓ.ም በቁጥጥር ሥር የዋሉት ሁለት ተጠርጣሪዎች ላይ ምርመራ እያጣራ መሆኑን የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ገልጿል። ባዳዎች እና ባንዳዎች ተቀናጅተው የሀገራችንን ሰላምና ደኅንነት ለማደፍረስ ፣ሀገራችን እያካሄደች ያለችውን ልማትና ዕድገት ለማደናቀፍ በተለያዩ ጊዜ ሲንቀሳቀሱ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው ይታወቃል። አሁን ላይም እነዚህ የጠላት ኃይሎች በሀገራችን ላይ አደጋ ለማድረስ እየተንቀሳቀሱ በመሆናቸው የፀጥታ ኃይሉ የጀመረውን ኦፕሬሽን አጠናከሮ እንደሚቀጥል እየገለፀ ኅብረተሰቡም ከፀጥታ ኃይሉ ጋር በመተባበር የተለመደውን ድጋፍ እንዲያደርግ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ጥሪውን አቅርቧል።
በአማራ ክልል የቀድሞ ታጣቂዎች የሰላምን ጥሪ ተቀብለው እንዲመጡ ህብረተሰቡ ጠንካራ ተሳትፎ እያደረገ ነው - ሌተናል ጀነራል ሹማ አብደታ
Jan 14, 2026 152
ደብረብርሃን፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የቀድሞ ታጣቂዎች የሰላምን ጥሪ ተቀብለው እንዲመጡ በማድረግ ሂደት ህብረተሰቡ ጠንካራ ትብብርና ተሳትፎ እያደረገ መሆኑን በሀገር መከላከያ ሰራዊት የልዩ ዘመቻዎች ዕዝ አዛዥ ሌተናል ጀነራል ሹማ አብደታ ተናገሩ። በሰሜን ሸዋ ዞንና በደብረብርሃን ከተማ አስተዳደር ለሚገኙ የቀድሞ ታጣቂዎች በደብረ ብርሃን ስልጠና ማዕከል የተሃድሶ ስልጠና እየተሰጠ ይገኛል። ሌተናል ጀነራል ሹማ አብደታ፤ በደብረ ብርሃን የተሃድሶ ስልጠና ማዕከል በስልጠና ላይ ለሚገኙ ለቀድሞ ታጣቂዎች ቀጣይ አቅጣጫ ላይ ያተኮረ ገለጻ አድርገዋል። ሌተናል ጀነራል ሹማ፤ በዚሁ ጊዜ ባስተላለፉት መልዕክትም የመንግስትን የሰላም አማራጭ በመቀበል ወደ ሰላም እየመጡ ያሉ የቀድሞ ታጣቂዎች ምስጋና ይገባቸዋል ብለዋል። የቀድሞ ታጣቂዎች የመንግስትን የሰላም ጥሪ ተቀብለው እንዲመጡ በማድረግ ሂደት ህብረተሰቡ ጠንካራ ትብብርና ተሳትፎ እያደረገ መሆኑን አስታውሰው ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተናግረዋል። በተሳሳተ መንገድ አሁንም በጫካ የሚገኙ ታጣቂዎች መንግስት ለሰላም የሰጠውን እድል እንዲጠቀሙበት አሳስበው ህግ የማስከበር ስራው ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። የአማራ ክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ምክትል ኃላፊ ደጀኔ ልመንህ፤ የሰላም አማራጭን በመቀበል ወደ ተሃድሶ ስልጠና የገባችሁ ሁሉ በቀጣይ በምትፈልጉት የልማት ዘርፍ እንድትሰማሩ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል። በክልሉ አሁን ላይ አስተማማኝ ሰላምና መረጋጋት መፈጠሩን አንስተው የዘላቂ ሰላም ግንባታ ስራዎች ተጠናክረው የሚቀጥሉ መሆኑንም ተናግረዋል። በተሃድሶ ስልጠና ላይ የሚገኙ የቀድሞ ታጣቂዎች በበኩላቸው ከስልጠናው በኋላ ወደ ሰላማዊ ህይወት በመመለስ የልማት አርበኛ እና የሰላም አምባሳደር ለመሆን ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል። ከቀድሞ ታጣቂዎቹ መካከል አስቻለው ተፈሪ፣ አበበ ወርቁ እና አስቻለው ተሻለ፤ በተሳሳተ መንገድ ወደ ጫካ በመግባት ለህዝቡ እንግልትና ስቃይ ምክንያት መሆናቸውን አስታውሰው በመፀፀት ህዝብን ለመካስ መምጣታቸውን ተናግረዋል። ሌሎች በጫካ የሚገኙ ወገኖችም የመንግስትን የሰላም ጥሪ በመቀበል ከጥፋት መንገድ ወጥተው እንዲመጡ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።
በዞኑ ሰላም የማጽናት ስራው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ አድርጓል
Jan 14, 2026 104
መተማ፤ ጥር 6/2018 (ኢዜአ):- በምዕራብ ጎንደር ዞን ማህበረሰቡን በማሳተፍ በተከናወነ ሰላም የማጽናት ስራ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ ማድረጉን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። አስተዳደሩ በግማሽ ዓመቱ የተከናወኑ የመንግስትና የፓርቲ ስራዎች አፈፃፀም ግምገማ ዛሬ በመተማ ከተማ አካሂዷል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ በመድረኩ ላይ እንደገለጹት በዞኑ ማህበረሰቡን በማሳተፍ የአካባቢውን ሰላም ለማፅናት በተደረገ ሁሉን አቀፍ ጥረት አበረታች ውጤት ተገኝቷል። በዚህም ትራንስፖርትን ጨምሮ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳለጡ ማስቻሉን ጠቅሰዋል። የአካባቢውን የተፈጥሮ ሀብትና ፀጋ በመለየትና በማልማት የህዝቡን ዘላቂ ተጠቃሚነት በበለጠ ለማረጋገጥ መሰረት መጣሉንም ጠቁመዋል። በዘርፉ ለተገኘው ስኬት የፀጥታ ሃይሎች ህብረተሰቡን በማሳተፍ ያከናወኑት ተግባር ወሳኝ ድርሻ እንደነበረው አመልክተዋል። በብልፅግና ፓርቲ የዞኑ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ እንዳለው ማሩ በበኩላቸው፤ የተለያዩ የህዝብ መድረኮችን በማካሄድ ህዝቡ የሰላሙ ባለቤት እንዲሆን የሚያስችሉ ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል። ማህበረሰቡን በማሳተፍ የተገኘውን ሰላም አፅንቶ ለማዝለቅ የተጀመረውን ቅንጅታዊ አሰራርና ትብብር አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባ አመላክተዋል። በዞኑ ያለውን ሰላም በመጠቀም የበጋ መስኖና የተፋሰስ ልማት ስራዎችን በአግባቡ ለመደገፍና ለማከናወን ተችሏል ያሉት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ አቶ ጤናው ፋንታሁን ናቸው። በዞኑ ከ4 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በበጋ መስኖ እየለማ መሆኑን ለአብነት ጠቅሰዋል። በውይይት መድረኩ ላይ የዞኑ አመራር አካላት፣ የስራ ሃላፊዎችና ሌሎች ከፍተኛ ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ የሥራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁትን የስሪላንካ አምባሳደር አሰናበቱ
Jan 14, 2026 134
አዲስ አበባ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ የሥራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁትን በኢትዮጵያ የስሪላንካ አምባሳደር ታሻንታ ኩማራሲሪን አሰናብተዋል። ተሰናባቹ የስሪላንካ አምባሳደር ታሻንታ ኩማራሲሪ ሲሪላንካ እና ኢትዮጵያ ጠንካራ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን ገልጸዋል። የሁለቱ ሀገራት ዘመናዊ ግንኙነት እአአ በ1972 መመስረቱን ገልጸው፤ አሁን ላይ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በባህልና በሕዝብ ለሕዝብ ትስስር ያላቸው ግንኙነት ማደጉን ተናግረዋል። በተጨማሪም በኢነርጂ፣ በግብርና እና በቱሪዝም ዘርፍ ያላቸው ግንኙነት መጎልበቱን ጠቁመዋል፤ 200 የሚጠጉ ሲሪላንካውያን በኢትዮጵያ በተለያዩ ዘርፎች ተሰማርተው እየሰሩ እንደሚገኙ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እና ሲሪላንካ ግንኙነታቸውን ለማስፋት በርካታ እድሎች እንዳላቸውም ነው ጨምረው የተናገሩት። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ስሪላንካ ዋና ከተማ ኮሎምቦ ቀጥታ በረራ እንዲጀምር በመጠባበቅ ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል። ይህም በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን ትስስር የበለጠ ለማሳደግ፣ ለንግድ ልውውጥ፣ ለአየር መንገድ የጭነት አገልግሎት፣ ቱሪዝምንና እንደ ኢነርጂ ያሉ ሌሎች ዘርፎችንም እንደሚያስፋፋ አመላክተዋል። በተጨማሪም በግብርና፣ የከበሩ ድንጋዮችና ጌጣጌጥ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር እየተሰራ መሆኑንም አንስተዋል።
ሀገራዊ ምክክሩ ችግሮችን በምክክር ለመፍታት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው
Jan 14, 2026 127
ጅግጅጋ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ምክክሩ ችግሮች በምክክር እንዲፈቱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። ሀገራዊ ምክክሩ ያላግባቡ ጉዳዮች ላይ በሰለጠነ መንገድ በመምከር ለሀገር ዘላቂ ሰላም፣ አንድነትና ብሄራዊ መግባባት መፍጠርን ዓላማ አድርጎ እየተካሄደ ነው። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ከዝግጅት እስከ አጀንዳ የማሰባሰብ የምክክር ምእራፍ ድረስ ለዋናው ምክክር ግብዓት የሚሆኑ የተለያዩ ተግባራትን ሲያከናውን ቆይቷል። በተለይም በአጀንዳ የማሰባሰብ የምክክር ምዕራፍ ላይ ዜጎች በጋራ ጉዳዮቻቸው ላይ በመምከር እና አጀንዳ በመስጠት በንቃት መሳተፋቸውን የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን መግለጹ ይታወሳል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የጅግጅጋ ከተማ ነዋሪዎች፤ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ከመነሻው የምክክር ሂደቶቹን አካታች እና አሳታፊ በማድረግ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ሲያሳትፍ ቆይቷል ብለዋል። በምክክሩ ዙሪያም ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፎ እና ግንዛቤ እንዲኖራቸው በማድረግ እያከናወነ ያለው ሥራ የሚበረታታ ነው ብለዋል። በዚህም ሀገራዊ ምክክሩ በሀገሪቱ የነበሩ ችግሮች በምክክር እንዲፈቱ ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለው ነዋሪዎቹ ተናግረዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል አቶ አብዱራህማን መሀመድ፤ ሀገራዊ ምክክሩ የጋራ አጀንዳ በማሰባሰብ፤ ችግሮችን በምክክር በመፍታትና አዲስ ባህል ለማዳበር ያግዛል ብለዋል። ይህም በሀገሪቱ የጋራ ትርክት ለመገንባት በሚደረገው ጥረቶች የማይናቅ አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ተስፋ ማድረጋቸውን ገልጸዋል። አቶ አደን ዩሱፍ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በሀገሪቱ እያከናወነ ያለው የምክክር ሂደቶች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን በማካተት የተከናወነ በመሆኑ የሚደነቅ ተግባር መሆኑን ተናግረዋል። በሀገሪቱ ያሉ አለመግባባቶችን በሠለጠነ መንገድ ለመፍታት የምክክር ሥራው ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትም ገልጸዋል። አቶ መላኩ ባልቻ በበኩላቸው፤ ሀገራዊ ምክክሩ ለሀገሪቱ የእድገት ጉዞ የላቀ ሚና እንዳለው ጠቅሰው፤ በተለይም መግባባትን በመፍጠር የኢትዮጵያን ብልጽግና ጉዞ ለማፋጠን ያስችላል ብለዋል። ሠላም ለሀገሪቱ እድገት ወሳኝ መሆኑን ተናግረው፤ በተለይም የታቀዱ የልማት ሥራዎችን ከግብ ለማድረስ ሀገራዊ ምክክሩ ከፍተኛ አስተዋፅኦ እንዳለው ተናግረዋል።
ሀገራዊ ምክክሩ በስኬት እንዲጠናቀቅ ተሳትፏችንን እናጠናክራለን
Jan 14, 2026 112
አዳማ ፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ምክክሩ በስኬት ተጠናቆ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን በምክክር ሂደቱ ውስጥ የምናደርገውን ተሳትፎ እናጠናክራለን ሲሉ አባ ገዳዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች እና ሀዳ ሲንቄዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በ11 ክልሎች እና 2 የከተማ አስተዳደሮች፣ በፌዴራል ደረጃ እንዲሁም በውጭ ሀገራት ከሚኖሩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ባለድርሻ አካላት ዘንድ አጀንዳ የማሰባሰብ ስራ ሰርቷል። በአጀንዳ የማሰባሰብ የምክክር ምዕራፉም በሀገራቸው ጉዳይ ላይ መሳተፍ የሚገባቸው ባለድርሻ አካላት ተገናኝተው በጋራ ጉዳዮቻቸው ላይ የመከሩ ሲሆን በሂደቱ ሀገር በቀል የግጭት አፈታት ስርዓት ውስጥ ትልቅ ሚና ያላቸው ባለድርሻ አካላትም መሳተፋቸውን የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን መግለጹ ይታወሳል። በኦሮሚያ ክልልም በሀገራዊ ምክክር ሂደቱ በስፋት ተሳትፎ ካደረጉ የህብረተሰብ ክፍሎች መካከል አባ ገዳዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች እና ሃዳ ሲንቄዎች ይጠቀሳሉ። ኢዜአ ያነጋገራቸው በአዳማ ከተማ የሚገኙ አባ ገዳዎች፣ የአገር ሽማግሌዎች እና ሃዳ ሲንቄ ሀገራዊ ምክክሩ በስኬት ተጠናቆ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን ያላቸውን ተሰሚነት ተጠቅመው በምክክር ሂደቱ ውስጥ የሚወጡትን ተሳትፎ እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። በአዳማ ከተማ የአባገዳ ክፍለ ከተማ ባህላዊ ፍርድ ቤት ሰብሳቢ ፈይሣ መገርሳ እንደገለፁት፤ሀገራዊ ምክክሩ የነበሩ ቁርሾዎችና ቅራኔዎች የሚፈቱበት ሁነኛ መፍትሔ ነው። እስካሁን በተደረጉ የምክክሩ ሂደቶችም የሀገር ሽማግሌዎች፣ የኃይማኖት አባቶች፣ አባ ገዳዎች፣ ሃዳ ሲንቄዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተሳትፎ ሲያደርጉ መቆየታቸውን ገልጸዋል። በአዳማ በተካሄደው የአጀንዳ ማሰባሰብ ምዕራፍ ላይ በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን የሚያግዙ ጠቃሚ ሀሳቦችን ማቅረባቸውን አስታውሰው፤ አሁንም ሂደቱ ፍጻሜውን እስኪያገኝ ድረስ የሚጠበቅባቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል። የምክክሩ ሂደት ውጤታማ እንዲሆን የድርሻችንን እየተወጣን ነው ያሉት ሰብሳቢው፤ ግጭቶች እና አለመግባባቶች ተወግደው ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን እስከ ፍጻሜው ተሳትፏችንን እናጠናክራለን ብለዋል፡፡ የሀገር ሽማግሌው አቶ ድሪባ ጫላ በበኩላቸው፤ በክልል ደረጃ በአዳማ ከተማ በተካሄደው የምክክር ምዕራፍ ተሳትፈው አብሮነት እና አንድነትን የሚያጠናክሩ ሀሳቦች ማንሳታቸውን ተናግረዋል። በተለይም ባህላዊ የግጭት አፈታት ስርዓቶችን በመጠቀም በየአካባቢው ላሉ ችግሮች ዘላቂ መፍትሔ መስጠት እንደሚገባ አመልክተው የምክክሩ ሂደት እንዲሳካ እንደ ሀገር ሽማግሌ ሚናችንን እናጠናክራለን ብለዋል። በቀጣይ በሚካሄደው ብሔራዊ ምክክር የሚሳተፉ አካላት ኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላም የሰፈነባት ሀገር እንድትሆንና ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሀሳቦች ላይ ማተኮር አለባቸው ያሉት ደግሞ የአገር ሽማግሌ አቶ ጥላሁን ራጎ ናቸው። ምክክሩ ችግሮቻችንን የምንፈታበት፣ የወደ ፊቷ ኢትዮጵያ የተሻለች እና ለሌሎች ምሳሌ እንድትሆን ምክክሩ ውጤት እስኪያመጣ ድረስ የሚያደርጉትን ተሳትፎ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። ሃዳ ሲንቄ ብርቄ ከበደ በበኩላቸው፤ እየተካሄደ ያለው ሀገራዊ ምክክር ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደረግ መፍትሄ ይዞ የሚመጣ በመሆኑ ሁሉም ለምክክሩ ስኬታማነት የድርሻውን ማጠናከር አለበት ብለዋል።
የብልጽግና ፓርቲ በመደመር እሳቤ ጠንካራ ሀገረ መንግስት የመገንባት ጥረት ውጤት እየተገኘበት ነው
Jan 14, 2026 106
ሆሳዕና፤ ጥር 6/2018(ኢዜአ)፦ የብልጽግና ፓርቲ በመደመር እሳቤና በህብረ ብሔራዊ አንድነት ጠንካራ ሀገረ መንግስት የመገንባት ጥረት ውጤት እየተገኘበት መሆኑን የፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንትና በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርአት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ አደም ፋራህ ገለጹ። የብልጽግና ፓርቲ የበጀት ዓመቱ የስድስት ወራት ሥራዎችን አፈጻጸም የሚገመግም መድረክ በሆሳዕና ከተማ ማካሄድ ጀምሯል፡፡ በሀገሪቷ እየተከናወኑ የሚገኙ ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎች የኢትዮጵያን እድገትና ማንሰራራት እውን የሚያደርጉ ናቸው በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የፓርቲው ምክትል ፕሬዚዳንትና በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርአት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ አደም ፋራህ፤ በመደመር እሳቤና በህብረ ብሔራዊ አንድነት የብልጽግና ፓርቲ ጠንካራ ሀገረ መንግስት የመገንባት ጥረት የተሳካ ውጤት እየተገኘበት መሆኑን ገልጸዋል። አሰባሳቢ ትርክትን በማጎልበት ለሁሉም ዜጎች የምትመች የበለጸገች ሀገር በመገንባት ለተተኪው ትውልድ ለማስተላለፍ ዘመን ተሻጋሪ የልማት አሻራዎች እንዲቀመጡ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።፡ በኢትዮጵያ ጠንካራ ተቋም የመገንባት እንዲሁም ፈጠራንና ፍጥነትን መሰረት ያደረገ ጠንካራ አመራር በመፍጠር ረገድም ፓርቲው ስኬታማ ተግባራትን ማከናወኑን ገልጸዋል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታን በማጠናቀቅ ለስኬት በማብቃት ሌሎች ሜጋ ፕሮጀክቶችን እውን ለማድረግ እየተሰራ ስለመሆኑም አንስተዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያን ከመገንባት አንስቶ የአንድ እቅድና የአንድ ሪፖርት አካሄድን በመከተል የአመራሩና የአባላቱን አቅም የመገንባት ሥራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውንም ጠቅሰዋል። በ2018 በጀት ዓመት የህዝብን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ ተግባራት ለማከናወን ታቅዶ በእቅዱ መሰረት እስካሁን ስኬታማ ስራዎች ተከናውነዋል ብለዋል። የዛሬው መድረክም በተለያዩ ዘርፎች በተከናወኑ ተግባራት የተገኙ ስኬቶችን በመገምገም አጠናክሮ ለማስቀጠልና ቀጣይ ተግባራት ላይ ለመምከር የሚያስችል መሆኑንም አንስተዋል። በመድረኩ ላይ የሁሉም ክልሎችና የሁለቱ ከተማ አስተዳደሮች የብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ኃላፊዎችና የወጣት ክንፍ አመራሮች እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡
የአሰባሳቢ ትርክት ግንባታ ሀገራዊ አንድነትን የሚገነባና አብሮነትን የሚያጸና ነው
Jan 13, 2026 300
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ የአሰባሳቢ ትርክት ግንባታ ሀገራዊ አንድነትን የሚገነባና አብሮነትን የሚያጸና መሆኑ ተጠቆመ። ከጥር 3 እስከ 5 ቀን 2018 ዓ.ም በጅማ ከተማ ሲካሄድ የቆየው “የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት አስፈላጊነቱን ማረጋገጥና ተቋማዊ መርሆዎችን መዘርጋት” የተሰኘው ብሔራዊ ጉባዔ የጋራ መግባቢያ ሰነድ በማፅደቅ በስኬት ተጠናቋል። በአንጋፋው አርቲስት ጥላሁን ጉግሳ በተነበበው የጅማ ስምምነት መግለጫ ላይ እንደተገለጸው፤ ስምምነቱ የሀገሪቷን ውስብስብ ፖለቲካዊ ጉዞ በመገንዘብ ዘላቂ ሰላምና ዲሞክራሲያዊ ህጋዊነትን በጋራ ትርክትና ትውስታ ለመደገፍ ያለመ ነው። ኢትዮጵያ ብሔራዊ አንድነትን የሚያጠናክር የጋራ ትርክት እንደሚያስፈልጋት ስምምነት ላይ መደረሱ በመግለጫው ተመላክቷል። ይህ ትርክት ከላይ የሚጫን ሳይሆን በጋራ የሚፃፍና አካታች መሆን እንዳለበት ተረጋግጧል። የወደፊቱ የጋራ ትርክት ግንባታ አካታችነትን፣ የጋራ ባለቤትነትን፣ ብዝሃ ትውስታን ማክበርንና ከህገ-መንግስታዊ እሴቶች ጋር መጣጣምን መርህ ሊያደርግ እንደሚገባ በመግለጫው ተመላክቷል። ትርክቱ በፖሊሲና ህግ ማዕቀፎች፣ በተቋማዊ ቅንጅት፣ በአካዳሚያዊ ምርምርና በመገናኛ ብዙኃን ኃላፊነት የተደገፈ እንዲሆን አቅጣጫ ተቀምጧል። የጅማ ስምምነት መግለጫ የኢትዮጵያ አንድነት ዜጎች ራሳቸውን በሃገራቸው ትርክት ውስጥ በሚያዩበት የጋራ ታሪክ ላይ የሚመሰረት መሆኑን አረጋግጧል። በጉባዔው የመዝጊያ መርሐ ግብር መግለጫው በይፋ ፀድቋል። ሙሉ የስምምነቱ መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል፡- የጅማ ስምምነት መግለጫ መግቢያ እኛ ከጥር 3-5 2018 በጅማ የተካሄደው “የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት አስፈላጊነቱን ማረጋገጥና ተቋማዊ መርሆዎችን መዘርጋት” በሚል አርዕስት ከፌዴራልና ከክልል መንግስታት፣ ከህገ-መንግስታዊ ተቋማት፣ ከዩኒቨርሲቲዎችና የምርምር ተቋማት፣ ከሲቪል ማህበረሰብ፣ ከሃይማኖታዊ ተቋማት፣ ከመገናኛ ብዙኃን፣ ከግል ዘርፍ፣ ከወጣቶችና ከሴቶች አደረጃጀቶች እና ከገለልተኛ ምሁራን የተውጣጡ፤ የኢትዮጵያ የረጅም የስልጣኔ ታሪክ፣ የባህል ባለፀጋነትና የጋራ የሰላም፣ የክብር፣ የፍትህና የብልጽግና ምኞት እየተመራን በተከታታይ የተፈጠሩ ፖለቲካዊ ስምምነቶች፣ የተጋጩ የታሪክ ትርጓሜዎች እና የአንድነትና የመከፋፈል ዘመናት ያሉበትን የሀገራችንን ውስብስብ ፖለቲካዊ ጉዞ በጥልቀት ተገንዝበን፤ ዘላቂ ሰላም፣ ዲሞክራሲያዊ ህጋዊነትና ተግባራዊ መንግስትነት ብቻ ሳይሆን በፖሊሲና ተቋማዊ ማሻሻያ ፣ በጋራ ትርጉም፣ በጋራ ትውስታና በአንድ የሀገር አቀፍ ማዕቀፍ መደገፍ እንዳለበት በመገንዘብ፤ የኢትዮጵያ ብዝሃነት—ቋንቋዊ፣ ባህላዊ፣ ሃይማኖታዊ፣ መልከዓ ምድራዊና ታሪካዊ እውነታ ሲሆን የመከፋፈል ምንጭ ሳይሆን የጥንካሬ አቅም መሆኑን በመቀበል፤ እየተካሄደ ያለውን የብሔራዊ ውይይት ሂደት እንደ መሠረታዊ መድረክ በመገንዘብ፣ ነገር ግን ውይይት ብቻ በቂ እንዳልሆነ እና በተቋማዊ፣ በአእምሯዊና በመገናኛ ብዙሃን ማዕቀፎች መደገፍ እንዳለበት በመግለጽ፤ በአካባቢያዊ የኢትዮጵያ ፍልስፍናዊ ትሩፋቶች የተመሠረተ በልዩነት ውስጥ አብሮ መገንባት፣ መካተት እና የጋራ ኃላፊነትን የሚያጎላ— አመለካከት ተመርተን ይህንን የጅማ ስምምነት መግለጫ እንደ የጋራ ብሔራዊ ቁርጠኝነትና መመሪያ ሰነድ በዛሬው እለት በይፋ እናፀድቃለን። I. የጋራ ሃገራዊ ትርክት አስፈላጊነት 1. ኢትዮጵያ የሚከተሉትን ሚናዎች የሚያገለግል የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት እንደሚያስፈለጋት እናረጋግጣለን፦ o የተለያዩ የታሪክ ትውስታዎችን በአንድ የፖለቲካ ማህበረሰብ ውስጥ ማዋሃድ፤ o በክልሎችና ትውልዶች መካከል ሞራላዊና ሲቪክ ተስማሚነት መፍጠር፤ o ልዩነትን ሳያጠፋ ብሔራዊ አንድነትን ማጠናከር፤ o የመንግስታዊ ቅቡልነትን፣ ህገ-መንግስታዊነትንና ዲሞክራሲያዊ ልማዶችን መመርኮዝ። 2. የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት ከተጫነ ወይም ከሚያገልል ትርክት በመሠረቱ ይለያል፤ እርሱ፦ o በጋራ የሚፃፍ እንጂ ከላይ የሚጫን አይደለም፤ o አካታች እንጂ ደረጃዊ ወይም አስተዳደራዊ አይደለም፤ o ተለዋዋጭና የሚያድግ እንጂ የተገደበ ወይም የተስተካከለ አይደለም። 3. የእንዲህ ዓይነት የጋራ አካታች አሰራር እጦት የሚከተሉትን አደጋዎችን እንደሚያስከትል እንገነዘባለን፦ o የብሔራዊ ውይይት መበታተን፤ o ዜሮ-ድምር የፖለቲካ መስተጋብር፤ o ደካማ ተቋማዊ ቅቡልነት፤ o የማንወጣው የመተማመን እጦት እንዲሁም የመከፋፈልና የውድቀት አዙሪት II. የወደፊቱ የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት በመፍጠር ውስጥ ልንከተላቸው የሚገቡ መርሆዎች o አካታችነትና የጋራ ባለቤትነት – ሁሉም ማህበረሰቦች፣ ክልሎች፣ ትውልዶችና ማህበራዊ ቡድኖች በእኩል ክብርና ድምፅ መወከል አለባቸው። o በአንድ ማዕቀፍ ውስጥ ያለ ብዝሃ ትውስታ – የተለያዩ ታሪካዊ ልምዶችን፣ ቅራኔዎችን እና አስተዋጽኦዎችን ማክበር እንጂ አንዱን በሌላው ላይ ማበላለጥ ተገቢ አይደለም። o በክብር፣ በስነ-ምግባራዊ መደማመጥና የእርስ-በእርስ እውቅናና ቁርጠኝነት ላይ የተመሠረተ ውይይት o የጋራ ሃገራዊ ትርክቶች ከህገ-መንግስትና ከዲሞክራሲ እሴቶች ጋር በማጣጣም –የሰብዓዊ መብቶችን፣ እኩልነትንና የሕግ የበላይነትን የሚያጠናክሩ መሆን ይኖርባቸዋል። o ተቋማዊነትና ዘላቂነት የሚያረጋግጥ – በግለሰቦች ወይም በየዘመኑ ፖለቲካ ሳይሆን በዘላቂ ተቋማት ላይ የተመሠረተ እንዲሁም በታሪክ መከባበር ላይ ተመስርቶ በጋራ ኃላፊነት የሚመራ ወደፊትን የሚያመላክት መሆን ይገባዋል። III. የተቋማዊነት ማዕቀፎች የጋራ ሃገራዊ (የወል) ትርክት በሚከተሉት ዘርፎች የተቀናጀ ድጋፍ ያገኛል፦ o የፖሊሲና የህግ ማዕቀፎች – በልማት እስትራቴጂዎች፣ በሰላም ግንባታ ፖሊሲዎች፣ በሲቪክ ትምህርትና በህዝብ ንግግር መመሪያዎች ውስጥ መዋሃድ። o ተቋማዊ ቅንጅት – በሚኒስቴሮች፣ በህገ-መንግስታዊ ተቋማት፣ በክልል አስተዳደሮችና በውይይት አካላት መካከል ግልጽ ሚናና ቅንጅት መፍጠር o አእምሯዊና አካዳሚያዊ እርከን – የዩኒቨርሲቲዎች፣ የምርምር ተቋማትና የባህል ባለሞያዎች ሚና ማጠናከር። o የመገናኛ ብዙኃን ኃላፊነት – እውነተኛ፣ ሚዛናዊና አካታች ህዝባዊ ንግግር ማበረታታት። IV. አጋርነትና የሂደት ቁርጠኝነት o የመንግስት፣ የሰላምና የውይይት ኮሚሽኖች፣ የአካዳሚያ፣ የሲቪል ማህበረሰብ፣ የመገናኛ ብዙኃን፣ የወጣቶችና የሴቶች ተቋማት ሚና የሚገልጽ የአጋርነትና የሂደት ፍኖተ ካርታ እናበረታታለን። o ከውይይት ወደ ተቋማዊ መደራጀት የሚያመራ የደረጃ በደረጃ ሂደትን እንደግፋለን። o ይህንን ሃገራዊ ምክክር አጠናክሮ ለማስቀጠል የሰላም ሚኒስቴር፣ CRPP እና ጅማ ዩኒቨርሲቲ በቀጣይ ሂደት ዋና አመቻቾች መሆናቸውን እንረጋግጣለን። V. የትግበራና ክትትል ቁርጠኝነት o ይህን ስምምነት ወደ ተግባር ለመቀየር በፖሊሲ ማስተካከያ፣ በተቋማዊ ቅንጅትና በቀጣይ ብሔራዊ ውይይት እንተጋለን። o የፖለቲካ ድጋፍ፣ የሀብት ማሰባሰብ፣ የአቅም ግንባታና የጊዜያዊ ግምገማ ስርዓቶች እንዲተገበሩ እንጠይቃለን። o የጋራ ሃገራዊ ትርክት ቀጣይ፣ ከጊዜ ጋር ተሻሽሎ የሚያድግና ለዲሞክራሲያዊ ማሻሻያ ክፍት የሆነ ብሔራዊ ፕሮጀክት መሆኑን እናረጋግጣለን። መዝጊያ የጅማ ስምምነት ኢትዮጵያ አንድነቷ በትእዛዝ ሳይሆን እራሳቸው በሃገራቸውና በትርክቷ ውስጥ የሚያዩ ዜጎቿና በጋራ ታሪካቸው መሆኑን ያረጋግጣል። ጅማ—የውይይት፣ የልውውጥና የእድሳት ከተማ በመሆን ይህን ብሔራዊ ቁርጠኝነት የሚወክል ምልክት ሆና ትቆማለች!! ይህ የጋራ ስምምነት ጥር 5 ቀን 2018 ዓ.ም በጅማ ከተማ ፀደቀ፡፡
በአጎራባች አካባቢዎች ያለውን ሰላም በጋራ በመጠበቅ ልማት እንዲፋጠን እንሰራለን
Jan 13, 2026 119
ነቀምቴ ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ በአጎራባች አካባቢዎች ያለውን ሰላም በጋራ በመጠበቅ ልማት እንዲፋጠን እንሰራለን ሲሉ የኦሮሚያ እና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች አመራሮች ገለጹ። የኦሮሚያ እና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች የጋራ ሰላምና ልማት፣ የግጭት አፈታትና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ውይይት በነቀምቴ ከተማ ተካሄዷል። በውይይቱ ላይ የተገኙ የክልሎቹ ተወካዮች በአጎራባች አካባቢዎች ያለውን ሰላም በጋራ በመጠበቅ ልማትን ለማፋጠን እንደሚተጉ ገልጸዋል። የኦሮሚያ እና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች የጋራ ሰላምና ልማት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ ዲንሳ በየነ፣ ጽህፈት ቤቱ በአጎራባች አካባቢዎች ሰላምና ልማት እንዲጠናከር የተለያዩ ተግባራት እያከናወነ ይገኛል ብለዋል። በክልሎቹ የጋራ ጥረት በተወሰዱ እርምጃዎችም አካባቢው ሰላም የሰፈነበት እና የልማት ስራዎች ያለመቋረጥ የሚካሄዱበት መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም ህዝቡ ትኩረቱን በሙሉ ልማት ላይ ማድረግ እንዲችል እና የተፈጥሮ ሀብቱን ተጠቅሞ መለወጥ እንዲችል የአካባቢው አመራሮች የድርሻቸውን በአግባቡ እንደሚወጡ ገልጸዋል። ይህ የወንድማማችነት መድረክ በነቀምቴ ከተማ ላይ ሲዘጋጅ ከውይይት በዘለለ በአካባቢው ተጨባጭ ውጤት ለማምጣት ያስችላል ሲሉም አክለዋል። ኦሮሚያ ክልል ፀጥታ እና አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ኮሚሽነር አራርሳ መርዳሳ፣ የፀጥታ አካላት ከህብረተሰቡ ጋር በመሆን በሰሩት የተቀናጀ ስራ በክልሎቹ አዋሳኝ አካባቢዎች ሰላም መስፈኑን ተናግረዋል። ክልሎቹም ተቀናጅተው ልማት እና ሰላምን ለማስቀጠል የጀመሩት ጥረት የበለጠ የሚጠናከር መሆኑንም አስረድተዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የሰላምና ፀጥታ ምክትል ኃላፊ አቶ ኢሳም የሱፍ በበኩላቸው፤ ተቀራርቦ መስራት በየጊዜው የሚያጋጥሙ ችግሮችን በዘላቂነት ለመቅረፍ ያግዛል ብለዋል። በተለይም የሰላም መንገዶችን አሟጦ ከመጠቀም ጎን ለጎን ችግሮች ሲያጋጥሙ የህግ ማስከበር ስራዎችን በተቀናጀ መልኩ መፈጸም እንደሚገባም ተናግረዋል። በውይይት መድረኩ ላይ የሁለቱ ክልሎች የዞኖችና የወረዳ አመራሮች እንዲሁም የጸጥታ አካላት አመራሮች ተሳትፈዋል።
በኢትዮጵያ በየትኛውም አካባቢ ሰባተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ዝግጅት ተደርጓል
Jan 13, 2026 197
አዲስ አበባ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ በየትኛውም አካባቢ ሰባተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ዝግጅት መደረጉን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታወቀ። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሀገር አቀፍ የሕግ አውጪዎች የጋራ ምክክር መድረክ በሰባተኛው ሀገራዊ ምርጫ እና በሌሎች ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ እየተካሄደ ነው። በመርሀ ግብሩ ላይ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ፣ ምክትል አፈ ጉባዔ ሎሚ በዶ፣ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጂጌ (ዶ/ር)፣ የክልሎች አፈ ጉባኤዎችና ምክትል አፈ ጉባኤዎች ተገኝተዋል። በመድረኩ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ተስፋዬ ንዋይ "የሰባተኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ ዝግጅትና የምክር ቤቶች ሚና" በሚል ርዕስ የመወያያ ሰነድ አቅርበዋል። ምክትል ሰብሳቢው በገለፃቸው፤ ከየካቲት 7 እስከ መጋቢት 7 ቀን 2018 ዓ.ም በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች የመራጮች ምዝገባ እንዲከናወን እና የድምፅ መስጫው ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም እንዲሆን ቦርዱ መወሰኑን አስታውቀዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ይሄንን ታሳቢ በማድረግ የግብዓት ማሟላት፣ የስልጠናና ግንዛቤ የመፍጠሪያ የተለያዩ ዝግጅቶችን ማድረጉን ገልጸዋል። በዚህም ቦርዱ በአዋጅ በተሰጠው ስልጣን መሰረት ከመደበኛ የምርጫ ጣቢያዎች የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች፣ በሥራ ምክንያት በተለያየ ቦታ የሚገኙ ዜጎች፣ የሀገር መከላከያ ሰራዊት አባላት እና ሌሎች ልዩ የምርጫ ጣቢያ ሊቋቋምላቸው የሚገባ ስለሆነ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በትብብር መስራታቸውን ገልጸዋል። በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ከ50 ሺህ በላይ የምርጫ ጣቢያዎች እንደሚኖሩ የገለጹት ምክትል ሰብሳቢው፤ በአዋጁ መሰረት እያንዳንዱ የምርጫ ጣቢያ ከ 1 ሺህ 500 የማይበልጥ መራጭ መያዝ አለበት ብለዋል። በተሻሻለው አዋጅ ቁጥር 1162/2011 መሰረት የምርጫ ስራዎችን ዲጂታላይዝ በማድረግ ለቦርዱ አቅም የሚፈጥሩ ድንጋጌዎች መካተታቸውን ገልጸዋል። በዚህም የዕጩዎችና የመራጮች ምዝገባ እንዲሁም ሌሎች የቦርዱን ስራ ውጤታማ ሊያደርጉ የሚችሉና የቅሬታ አፈታት ስልቶች ማሻሻያ እንደተደረገባቸው ጠቅሰዋል። በአጠቃላይ ቦርዱ በኢትዮጵያ በየትኛውም አካባቢ ምርጫውን ማከናወን የሚያስችል ዝግጅት ማድረጉን ተናግረዋል። መራጮች በዲጂታል ወይም በአካል በመቅረብ መመዝገብ እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መተግበሪያ አማካኝነት ባሉበት ሆነው መመዝገብ የሚፈልጉ መራጮች የብሔራዊ መታወቂያ ሊኖራቸው እንደሚገባ ገልጸዋል። በቦርዱ የተመለመሉ የምርጫ አስፈፃሚዎች ከማንኛውም የፖለቲካ ፓርቲ ገለልተኛ የሆኑ ለስራው በቂ የትምህርት ዝግጅት ያላቸውና የአካባቢውን የስራ ቋንቋና ባህል የሚያውቁ መሆናቸውን ተናግረዋል።በመላ ሀገሪቱ ቢያንስ 318 ሺህ ምርጫ አስፈፃሚ እንደሚያስፈልግም አስታውቀዋል፡፡ የፖለቲካ ፖርቲዎች የፅሁፍና የቃል ፈተናውን ያለፉ የምርጫ አስፈፃሚዎችን ገለልተኝነት በተመለከተ አስተያየት እንዲሰጡ ተደርጓል ብለዋል።
ለ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የዜጎች ተሳትፎ እንዲጠናከር የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የላቀ ሚናቸውን ለመወጣት እየተዘጋጁ ነው
Jan 13, 2026 167
ወላይታ ሶዶ፤ ጥር 5/2018(ኢዜአ)፦ በግንቦት ወር ለሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የዜጎች ተሳትፎ እንዲጠናከር የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የላቀ ሚናቸውን ለመወጣት እየተዘጋጁ መሆኑን የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን አስታወቀ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የጠቅላላ ምርጫው ሂደት ነፃ፣ ፍትሐዊና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መልኩ እንዲካሄድ ከወዲሁ ዝግጅት እያደረገ መሆኑ ይታወቃል። ለምርጫው ሂደት የቦርዱ የተሟላ ዝግጅት እንዳለ ሆኖ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሲቪክ ማህበራትና አጠቃላይ የዜጎች ጠንካራ ተሳትፎ ወሳኝ ነው። በዚህም መሰረት የዜጎች የምርጫ ተሳትፎ እንዲጠናከር በማድረግ በኩል በተለይም የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ዝግጁነት ምን ይመስላል ሲል ኢዜአ የሚለከታቸው አካላትን አነጋግሯል። የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ምክትል ዳይሬክተር ፋሲካው ሞላ፤ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ሂደት ሁነኛ መሰረት በሆነው የምርጫ ሂደት የዜጎች ጠንካራ ተሳትፎ አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል። በዚህ ሂደትም ዜጎች በቂ ግንዛቤ አግኝተው በእውቀት ላይ ተመስርተው መብታቸውን መጠቀም እንዲችሉ ድርጅቶቹ የማስተማርና የማስገንዘብ ስራ ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። በዚሁ መሰረትም በመጪው ግንቦት ወር ለሚካሄደው 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የዜጎች ተሳትፎ እንዲጠናከር የሲቪክ ማህበራት የላቀ ሚናቸውን ለመወጣት እየተዘጋጁ መሆኑን አንስተዋል። በባለስልጣኑ የታቀፉ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ከቅድመ ምርጫ ጀምሮ አጠቃላይ ሂደቱ የተሳካ እንዲሆን እንደሚሰሩም ገልጸዋል። ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ለ54 የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምርጫን የመታዘብ፣ እንዲሁም ህብረተሰቡን ለማስተማር ፈቃድ በመስጠቱ ምህዳሩን አስፍቶልናል ያሉት ደግሞ የኦሮሚያ ክልል ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ታደሉ እጀታ ናቸው። ለምርጫው ሰላማዊ ሂደት ምክር ቤቱ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ለመወጣት መዘጋጀቱን በመግለጽ። ለምርጫ ሂደት መሳካት የዜጎች ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን በማንሳት በቂ ግንዛቤ ኖሯቸው እንዲሳተፉ ድርጅቱ ሚናውን ይወጣል ሲሉም አክለዋል። የሲዳማ ክልል ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ማስረሻ ክብረት፤ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በምርጫ ሂደት አወንታዊ አበርክቶ እንዲኖራቸው ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ገልጸዋል። በዚህም መሰረት የሲቪክ ማህበራት ሚናቸውን መወጣት የሚያስችል ዝግጁነት እንዳላቸውም ነው ጨምረው የተናገሩት። በአንድ ሀገር የምርጫ ሂደት ነፃ፣ ፍትሃዊ እና ዴሞክራሲያዊ እንዲሆን የሲቪክ ማህበራት ሚና የላቀ መሆኑ ይታመናል።