ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
በክልሉ የሚያጋጥሙ በሽታዎችን ፈጥኖ በመለየት ምላሽ መስጠት የሚያስችል የጤና ስርዓት የመዘርጋት ስራ ይጠናከራል
Jul 11, 2025 14
ባህርዳር፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በየጊዜው የሚያጋጥሙ በሽታዎችን ፈጥኖ በመለየት ምላሽ መስጠት የሚያስችል የጤና ስርዓት የመዘርጋት ስራ እንደሚጠናከር በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) ገለጹ። በአማራ ክልል ለቀጣይ አምስት ዓመታት የሚተገበር "የጤና ደህንነት ትግበራ /health security activity/" የተሰኘና የህብረተሰቡን ጤንነት የሚያስጠብቅና የሚያሻሽል ፕሮጀክት ዛሬ በባህር ዳር ከተማ ይፋ ተደርጓል። በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ፣ የክልሉ የማህበራዊ ዘርፍ አስተባባሪና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ ሙሉነሽ ደሴ(ዶ/ር) በወቅቱ እንደገለጹት በክልሉ የጤና ስርዓቱን ለማሻሻል የተለያዩ ጥረቶች እየተደረጉ ነው። በዛሬው እለት ይፋ የተደረገው ፕሮጀክትም በክልሉ በየጊዜው የሚያጋጥሙ የጤና ችግሮችን ለይቶ መፍታት የሚያስችል መሆኑን አስረድተዋል። ፕሮጀክቱ የበሽታ ቅኝት በማድረግ፣ በፍጥነት በመለየትና ለሚመለከተው አካል በማሳወቅ አፋጣኝ መፍትሄ ለመስጠት አጋዥ ሚና እንደሚጫወት ተናግረዋል። ፕሮጀክቱ የታለመለትን ግብ እንዲመታ የክልሉ መንግስትና ህዝብ አስፈላጊውን ድጋፍና ትብብር ያደርጋሉ ብለዋል። የአማራ ክልል የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር በላይ በዛብህ፤ ፕሮጀክቱ በክልሉ በተመረጡ 56 ወረዳዎች የሚተገበር ነው ብለዋል። በክልሉ በጤናው ዘርፍ የሚታዩ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት የቤተ ሙከራ አቅምን ማሳደግና የባለድርሻ አካላትን ተሳትፎ ማጎልበት ላይ በትኩረት እንደሚሰራ አስረድተዋል። "የጤና ደህንነት ትግበራ /health security activity/" ፕሮጀክት ምክትል ኃላፊ ዶክተር ኤልያስ ዋለልኝ በበኩላቸው ፕሮጀክቱ የአማራ ክልልን ጨምሮ በአፋርና በትግራይ ክልሎች የሚተገበር መሆኑን ተናግረዋል። በዚህም ፕሮጀክቱ ከሰው ወደ ሰው፣ ከእንስሳት ወደ ሰው፣ ከሰው ወደ እንስሳትና ከአካባቢ ወደ ሰው የሚተላለፉ በሽታዎችን አስቀድሞ በሚካሄድ ቅኝት በመለየት ለመከላከል አልሞ የሚሰራ ነው ብለዋል። በመድረኩ የክልልና የፌደራል የጤናው ዘርፍ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
በጌዴኦ ዞን የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ በትብብር እየተሰራ ነው - የዞኑ አስተዳደር
Jul 11, 2025 43
ዲላ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ በጌዴኦ ዞን የትምህርት ጥራትን ለማስጠበቅ ከህብረተሰቡ እና ከአጋር አካላት ጋር በትብብር የሚደረጉ ጥረቶች ተጠናክረው መቀጠላቸውን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። በዞኑ ዲላ ከተማ አስተዳደር በ40 ሚሊዮን ብር ወጪ የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ እየተከናወነ ነው። ግንባታው የዞኑ አስተዳደር ከዓለም አቀፉ የትምህርትና ባህል ተራድኦ ድርጅት(WECA) ጋር በመተባበር የሚከናወን ሲሆን ግንባታውን በተያዘው ዓመት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚደረግ ተመላክቷል። የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ(ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት በዞኑ የትምህርት ስብራትን በዘላቂነት ለመቅረፍና ጥራትን ለማስጠበቅ ከህብረተሰቡ እና ከአጋር ድርጅቶች ጋር በትብብር እየተሰራ ነው። በተለይ በተያዘው በጀት ዓመት በዞኑ 80 በመቶ የሚሆኑ ትምህርት ቤቶች ያሉባቸውን የመሰረተ ልማት ችግር በማሻሻል የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ ትኩረት እንደሚደረግ ገልጸዋል። የትምህርት ቤቱ ግንባታ በአጭር ጊዜ እንዲጠናቀቅ ክትትል የሚደረግ መሆኑን አንስተው የትምህርት ጥራትን በማረጋገጥ ሞዴል ትምህርት ቤት ከመፍጠር ባለፈ ደረጃውን ወደ አዳሪ ትምህርት ቤት ለማሳደግ መታቀዱንም ገልጸዋል። ትምህርት ቤት የእውቀት መገበያያ ብቻ ሳይሆን የትውልዱ የስብዕና ግንባታ ማዕከል መሆኑን ያነሱት ደግሞ የዓለም አቀፉ የትምህርትና ባህል ተራድኦ ድርጅት የቦርድ ሰብሳቢ ባንግ ቱንጋዋን ናቸው። ድርጅታቸው በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች የትምህርት መሰረተ ልማትን በማስፋፋት የትምህርት ጥራትን ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት እያገዘ ነው ብለዋል። በዲላ ከተማ ከዞኑ አስተዳደር ጋር በመተባበር የ2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከመገንባት ባሻገር በትምህርት ቤቱ የውጭ ቋንቋዎችን በማስተማር የትምህርት ስርዓቱን እየደገፈ መሆኑን ጠቁመዋል። የጌዴኦ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ ዘማች ክፍሌ በበኩላቸው የትምህርት ቤቱን የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ በተያዘው ዓመት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት ክፍት እንደሚደረግ ተናግረዋል። ይህም 13 መማሪያ ክፍሎችን ጨምሮ የአስተዳደርና የመጸዳጃ ህንጻዎችን እንዲሁም የስፖርት ማዘውተሪያ ስፍራዎችን ያካተተ ሲሆን ለዚህም ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ እንደሚደረግ ገልፀዋል። በአሁኑ ወቅትም አራት የመጀመሪያ ደረጃ የመማሪያ ክፍሎች ግንባታ መጠናቀቃቸውን አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ በስደተኞች አያያዝ አርዓያነት ያለው ተግባር እያከናወነች ነው
Jul 11, 2025 40
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በስደተኞች አያያዝ አርዓያነት ያለውና የሚደነቅ ተግባር እያከናወነች ነው ሲሉ በኢትዮጵያ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ረዳት ተጠሪ ዴቪድ ካርፕ ገለጹ፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ከሃያ ስድስት አገራት በተለያየ ምክንያት የመጡ ከ1 ሚሊዮን በላይ ስደተኞች እና ጥገኝነት ጠያቂዎችን በመቀበል ተገቢውን ጥበቃና ከለላ እየሰጠች ትገኛለች። በኢትዮጵያ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ረዳት ተጠሪ ዴቪድ ካርፕ፥ ኢትዮጵያ የዓለም አቀፍ የስደተኞች አያያዝ መርህን ባከበረ መልኩ ለስደተኞች አገልግሎት እየሰጠች እንደምትገኝ ለኢዜአ ገልጸዋል። ስደተኞች ባሉባቸው አካባቢዎች የመንገድ፣ የውሃ፣ የመብራት፣ የትምህርት፣ የጤና እና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ተገንብተው አገልግሎት እንዲያገኙ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ስደተኞች ከተቀባዩ የህብረተሰብ ክፍል ጋር በማስተሳሰር በስራ እድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ መሆኑንም እንዲሁ፡፡ ይህም ኢትዮጵያን ለስደተኞች ከፍተኛ ትኩረት ከሚያደርጉ እና ክብር ከሚሰጡ የዓለም ሀገራት መካከል አንዷ እንደሚያደርጋት አንስተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ በስደተኞች አያያዝ ዙሪያ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት ለሌሎች የዓለም አገራት አርዓያ እንደሚሆኑም ጠቁመዋል፡፡ ረዳት ተጠሪው አክለውም የኢትዮጵያ መንግስትና ህዝብ ለዚህ ተግባራቸው ምስጋና ይገባቸዋል ነው ያሉት፡፡ በቀጣይ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ኮሚሽን በስደተኞች አያያዝ ላይ ያለውን ቅንጅታዊ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል፡፡
የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከህሊና እርካታ ባለፈ ማኅበራዊ ትስስር እያጎለበተ መጥቷል - አቶ መለስ አለሙ
Jul 11, 2025 39
ሐረር፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከህሊና እርካታ ባለፈ ማኅበራዊ ትስስርን እያጎለበተ መምጣቱን በብልፅግና ፓርቲ የዋና ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለስ ዓለሙ ተናገሩ። በኦሮሚያ ክልል አምስት ሚሊዮን ሴቶች የሚሳተፉበት የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በማያ ከተማ ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በፕሮግራሙ ማስጀመሪያ ላይ የተገኙት በብልፅግና ፓርቲ የዋና ጽሕፈት ቤት የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መለስ ዓለሙ እንደገለጹት በዘንድሮው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ሴቶችና ወጣቶች፣ የሲቪክ ማህበራት፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችና ሌሎች የሚሳተፉበት የተለያዩ ተግባራት ይከናወናሉ። በፕሮግራሙ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላን ጨምሮ የአቅመ ደካማ መኖሪያ ቤቶች እድሳት፣ የድጋፍና እንክብካቤ እንዲሁም ሌሎች ስራዎች ይከናወናሉ ብለዋል። እነዚህ የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች ከህሊና እርካታ ባለፈ ወንድማማችነትንና ማህበራዊ ትስስርን እያጠናከሩ በመምጣታቸው ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸዋል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የሴቶች ክንፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ሳሚያ አብደላ እንደገለጹት በክልሉ አምስት ሚሊዮን ሴቶች የሚሳተፉበት የክረምት በጎ ፈቃድ ተግባራት ተጀምረዋል። በመርሃ ግብሩም የአቅመ ደካማ መኖሪያ ቤት እድሳት፣ የደም ልገሳ፣ ማዕድ ማጋራት፣ የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላን ጨምሮ 11 የበጎ ፈቃድ አገልግሎቶች እንደሚከናወኑ ገልጸው ይህም ሴቶች እርስ በእርስ እንዲደጋገፉ ዕድል ይፈጥራል ብለዋል። በኦሮሚያ ክልል የማያ ከተማ ምክትል ከንቲባ ታደለ ንጉሴ በበኩላቸው በከተማ መስተዳድሩ በሚከናወነው የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ300 ሺህ በላይ በጎ ፈቃደኞች በ34 የክረምት በጎ ፈቃድ ተግባራት እንደሚሳተፉ ጠቁመዋል። የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራዎች ህብረተሰቡን እየደገፈና የወጣቶችን ተሳትፎና የመረዳዳት ባህልና እሴትን እያጎለበተ መምጣቱን ገልጸዋል። ከታማሚ ልጃቸው ጋር በፈረሰ ቤታቸው ውስጥ ሲኖሩ ለችግር ተጋልጠው እንደነበር ያስታወሱት ደግሞ በማያ ከተማ አስተዳደር የአደሌ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ዙቤዳ ቃሲም ናቸው። አሁን ላይ ይህን ችግራቸውን የበጎ ፈቃደኞች ተመልክተው ቤታቸው በማደሳቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል። መኖሪያ ቤታቸው ከማርጀቱ የተነሳ ጉዳት እንዳይደርስባቸው ለህይወታቸው ይሰጉ እንደነበር የገለጹት ደግሞ ሌላው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ተጠቃሚው አቶ ሸሪፍ ኢብራሂም ናቸው። ይህን ችግራቸውን በመረዳት የማያ ከተማ መስተዳድርና ነዋሪዎች ቤታቸውን በመገንባታችው መደሰታቸውን ተናግረዋል። በፕሮግራሙ የብልፅግና ፓርቲ ሴቶች ክንፍና ሌሎች የፌደራልና የክልል የብልፅግና ፓርቲ የዴሞክራሲ ባህል ግንባታ ዘርፍ አመራሮች ተገኝተዋል።
ኢትዮጵያ ያሏትን የቱሪዝም ፀጋዎች ለአለም በማስተዋወቅ የዘርፉን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ የባለድርሻ አካላት ቅንጅት ያስፈልጋል - የዘርፉ ባለሙያዎች
Jul 11, 2025 57
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡-ኢትዮጵያ ያሏትን የቱሪዝም ፀጋዎች ለአለም በማስተዋወቅ የዘርፉን ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው ሊሰሩ እንደሚገባ የዘርፉ ባለሙያዎች ገለፁ። በኢትዮጵያ በአገር በቀል ሪፎርሙ ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰሩ ካሉ አምስት የኢኮኖሚ ምሰሶዎች መካከል አንዱ ቱሪዝም ነው። የአዳዲስና ነባር የቱሪዝም መዳረሻዎች ልማት እየተከናወነ ሲሆን ዘርፉ ለአገሪቱ ኢኮኖሚ የሚያበረክተውን ሚና ለማሳደግ የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ ይገኛሉ። ይሄንንም በማስመልከት አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የቱሪዝም ባለሙያዎች እንዳሉት መንግስት የሰጠው ትኩረት ለዘርፉ ከፍተኛ መነቃቃትን መፍጠር ችሏል። የታላቁ ኢትዮጵያ አስጎብኚ ድርጅቶች ማህበር አባልና የፕሌዠር ኢትዮጵያ አስጎብኚና የጉዞ ወኪል ባለቤት ናሆም አድማሱ እንዳሉት ኢትዮጵያን በቱሪዝም ዘርፍ የበለጠ ከፍ ማድረግ የሚያስችል አቅም ተፈጥሯል። ሀገሪቱ ያላትን በርካታ የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ የመስህብ ቦታዎች በማስተዋወቅና መልካም መስተንግዶን ለጎብኚዎች በመስጠት ከዘርፉ የሚገኘውን ተጠቃሚነት ማሳደግ ያስፈልጋል ብለዋል። የጉዞና ጉብኝት ጋዜጠኛ ሄኖክ ስዩም በበኩሉ በአሁኑ ሰዓት መንግስት ከመቼውም ጊዜ በላይ ለቱሪዝም ዘርፉ ትኩረት ሰጥቶ መስራቱን ተናግሯል። የቱሪዝም መዳረሻ ልማት ስራዎች በመላው ሀገሪቱ እየተከናወኑ መሆናቸውንና ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት ለቱሪዝም መነቃቃት አስተዋፅኦ እያበረከቱ መሆኑን ተናግሯል። ለቱሪስቶች ምቹ ሁኔታን መፍጠር የሚያስችሉ የቱሪዝም መዳረሻ ልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን የገለጹት ደግሞ የአዲስ አበባ ሆቴልና ቱሪዝም ባለሙያዎች ማህበር ኤክስክዩቲቭ አባል ወንድምዬ አዋሽ ናቸው። ኢትዮጵያ ያሏትን የቱሪዝም ፀጋዎች ለአለም በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኘውን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ማሳደግ ላይ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል። ጠንካራ የቱሪዝም ዲፕሎማሲ ያላት አገርን ለትውልድ ለማስተላለፍም ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው ሊሰሩ እንደሚገባ ተናግረዋል። የቱሪዝም ዘርፉን ተጠቃሚነትና ዘላቂነት ለማረጋገጥ የዘርፉ ተዋንያን መልካም ስነምግባርን በመላበስ በቅንጅት መስራት ላይ ትኩረት እንዲሰጡም እንዲሁ።
በምዕራብ ወለጋ ዞን በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ10 ሺህ በላይ የአቅመ ደካማ ቤቶች ግንባታና እድሳት ይከናወናል
Jul 11, 2025 56
ጊምቢ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡-በምዕራብ ወለጋ ዞን በክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ10 ሺህ በላይ የአቅመ ደካማ ቤቶች ግንባታና እድሳት ለማከናወን ወደ ተግባር መገባቱን የዞኑ ሴቶችና ህፃናት ጉዳዮች ጽህፈት ቤት አስታቀ። በጽህፈት ቤቱ የሴቶች ንቅናቄና ተሳትፎ የማስፋት ቡድን መሪ አቶ ኤፍሬም ጃለታ፣ በዞኑ በዘንድሮ በጎ ፈቃድ አገልግሎት የአረንጓዴ አሻራ፣ የአቅመ ደካሞች ቤት ዕድሳትና ግንባታ፣ የማጠናከሪያ ትምህርት፣ ደም ልገሳ፤ የትምህርት ቁሳቁስ ድጋፍና ሌሎች ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን ገልጸዋል። የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራውን ለማሳካትም ወጣቶችን ጨምሮ ለሁሉም ባለድርሻ አካላት የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራ ተሰርቷል ብለዋል። የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ለማሳካትም የዞኑ ወጣቶችና ሴቶች አደረጃጀቶችን ጨምሮ አቅም ያላቸው ነዋሪዎች እንደሚሳተፉ ተናግረዋል። በዞኑ ባለፉት ዓመታት በተከናወኑ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራዎች የበርካታ ሰዎችን ህይወት ከችግር ማውጣት መቻሉን አንስተዋል፡፡ ይህንን በበለጠ በማጠናከር ከ6 ሺህ 489 በላይ ያረጁና 4 ሺህ 326 አዲስ የአቅመ ደካማ ቤቶች ግንባታና እድሳት ለማከናወን ወደ ተግባር መገባቱን አስታውቀዋል። በአጠቃለይ በዚህ ክረምት ወራት በዞኑ በተለያዩ የልማት ዘርፎች በሚከናወን የበጎ ፈቅድ አገልግሎት ይወጣ የነበረን ከፍተኛ የመንግስት ገንዘብ መታደግ ይቻላል ብለዋል። በክረምቱ በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራው ከሚሳተፉት መካከል ወጣት ዱላ ቸርነት፤ በበጎ ፈቃድ አገልግሎቱ የተቸገሩ ወገኖችን በማገዝ የዜግነት ግዴታውን ለመወጣት መዘጋጀቱን ገልጿል። በበጎ ፈቃድ የሚከናወኑ ስራዎች ላይ በመሰማራት ሀገርንና የተቸገሩ ወገኖችን ማገልገል ደስታ የሚሰጥ ተግባር እንደሆነም ጠቅሰዋል፡፡ በዞኑ በየዓመቱ የሚከናወኑ የክረምት ወቅት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ሥራ ሲሳተፍ መቆየቱን የተናገረው ደግሞ የጊምቢ ከተማ ነዋሪ ወጣት አለማየሁ ዳቃ ነው፡፡ በዚህ ክረምትም ከሌሎች ወጣቶች ጋር በመሆን በተለያዩ በጎ ፈቃድ አገልግሎት ስራዎች ለመሳተፍ መዘጋጀቱን ገልጿል።
መንግሥት በሰቆጣ ቃል ኪዳን እና በትምህርት ምገባ መርሐ ግብር ለትውልድ ግንባታ አመርቂ ስራዎችን እያከናወነ ነው
Jul 11, 2025 50
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦መንግሥት በሰቆጣ ቃል ኪዳን እና በትምህርት ምገባ መርሐ ግብር ለትውልድ ግንባታ አመርቂ ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን የኢትዮጵያ የትምህርት ቤቶች ምገባ ኢኒሼቲቭ ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬዓለም ሽባባው ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "ከራዕይ ወደ ተግባር፤ የኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ" በሚል መሪ ሀሳብ በኢትዮጵያ ሥርዓተ ምግብ ላይ ያተኮረ ውይይት አካሂዷል፡፡ በዚሁ ወቅት የኢትዮጵያ የትምህርት ቤቶች ምገባ ኢኒሼቲቭ ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬዓለም ሽባባው እንዳሉት፥የኢትዮጵያ መንግስት ትልልቅ ኢኒሼቲቮችን በመቅረፅ ለትውልድ ግንባታ በርካታ ስራዎችን እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ከዚህም ውስጥ የትምህርት ቤት ምገባ እና የሰቆጣ ቃል ኪዳን ተጠቃሽ መሆናቸውን ያነሱት ዳይሬክተሯ፤ ከቅድመ መደበኛ እስከ 8ኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች የምገባ መርሐ ግብር እያከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡ ለአብነትም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በቀን ሁለት ጊዜ ከ800 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በመመገብ ላይ እንደሚገኙ ጠቁመው፤ ከ13ሺህ በላይ ለሆኑ እናቶችም የስራ ዕድል መፈጠሩን ገልጸዋል፡፡ የምገባ መርሃ ግብሩ መንግስት የተገበራቸው ትልልቅ ኢኒሼቲቮች ውጤታማ መሆናቸውን አንዱ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የተማሪዎች መጠነ ማቋረጥና ማርፈድ ማስቀረት ማስቻሉን ተናግረዋል፡፡ በሰቆጣ ቃልኪዳን ህጻናት ከጽንስ ጀምሮ ተመጣጣኝ ምግብ እንዲያገኙ በማስቻል የነገዋን ኢትዮጵያ በመገንባት ላይ እንደሚገኝም ጠቁመዋል፡፡ የሰቆጣ ቃልኪዳን በማስፋፋት ምዕራፍ ትግበራው በ2017 በጀት ዓመት በ334 ወረዳዎች የተተገበረ ሲሆን በዚህም በሚሊዮን የሚቆጠሩ የሚያጠቡና ነፍሰጡር እናቶች እንዲሁም በርካታ ህጻናት ተጠቃሚ መሆናቸው ይታወቃል።
በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ224 ሚሊዮን ብር በላይ ከምዝበራ ማዳን ተችሏል
Jul 11, 2025 48
ቦንጋ ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡- በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በተከናወነ ሙስናን የመከላከል ስራ ከ224 ሚሊዮን ብር በላይ የመንግሥትና የህዝብ ሃብት ከምዝበራ ማዳንና ማስመለስ መቻሉን የክልሉ ስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ገለጸ። በበጀት ዓመቱ በክልሉ 4 ሺህ 200 የመንግስት ሰራተኞችን በመመዝገብ የምስክር ወረቀት መሰጠቱም ተገልጿል። የክልሉ ስነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ኮሚሽነር ሙሉሰው ዘውዴ ለኢዜአ እንደገለፁት፣ በተገባደደው በጀት ዓመት በትውልድ ስነ-ምግባር ግንባታና የአስቸኳይ ሙስና መከላከል ስራ ትኩረት ተደርጎ ሲሰራ ቆይቷል። እንዲሁም በአሰራር ስርዓት ጥናትና በሙስና መረጃ ማደራጀትና መተንተን እንዲሁም በተቋም ግንባታ በርካታ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል። በዓመቱ 729 ጥቆማዎችን በጽሁፍ፣ በስልክ፣ በአካልና በተለያዩ የመረጃ መቀበያ አማራጮች መቀበሉን ጠቁመዋል። ጥቆማዎቹም በሀሰተኛ ሰነድ መጠቀም፣ በሰነድ ማጭበርበር፣ በሀብት ምዝበራ፣ ስልጣንን ያለ አግባብ መጠቀም፣ ምንጩ ያልታወቀ ሀብት ማፍራትና በሌሎች ጉዳዮች ላይ ያተኮሩ እንደነበሩም ኮሚሽነር ሙሉሰው ገልፀዋል። ከቀረቡት ጥቆማዎች ውስጥ 292ቱ በአስቸኳይ ሙስና መከላከል እንዲሁም 124ቱ ላይ ማስረጃን በማደራጀትና በመተንተን ለፍትሕ አካላት የማስተላለፍ ስራ ተሰርቷል ብለዋል። ኮሚሽነሩ አያይዘውም 202 ጥቆማዎች በአስተዳደራዊ እርምጃ ምላሽ የተሰጠ ሲሆን ቀሪ 27 የምክርና የህግ ከለላ መስጠት ተችሏል ነው ያሉት። 292 ጥቆማዎች ላይ በተሰራው አስቸኳይ የሙስና መከላከል ስራ ሊመዘበር የነበረን ከ178 ሚሊዮን 871 ሺህ ብር በላይ ማዳን መቻሉን ኮሚሽነር ሙሉሰው ተናግረዋል። እንደ ኮሚሽነር ሙሉሰው ገለጻ ከገንዘብ በተጨማሪ ከ166 ሺህ 708 ካሬ የከተማ እንዲሁም ከ505 ሄክታር በላይ የገጠር መሬት ማዳን ተችሏል። በኦዲት ግኝት ተመዝብሮ የነበረን ሀብት ለማስመለስ በተደረገው ጥረትም ከ45 ሚሊዮን 618 ሺህ ብር በላይ እንዲሁም በዓይነት የተለያዩ የመንግስት ንብረትና ቁሳቁሶችን የማስመለስ ስራ መሰራቱን ገልፀዋል። ይህም በአጠቃላይ በተሰራው ሙስናን የመከላከል ስራ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ224 ሚሊዮን 489 ሺህ ብር በላይ በገንዘብና በዓይነት የመንግሥትና የህዝብ ሃብትን ከምዝበራ ማዳንና ማስመለስ መቻሉን ነው የገለጹት። በተጨማሪም በተገባደደው በጀት ዓመት 4 ሺህ 200 የመንግስት ሰራተኞችን በመመዝገብ የምስክር ወረቀት መሰጠቱን ጠቁመው የመረጃውን ትክክለኛነት በማረጋገጥ ግልፀኝነትና ተጠያቂነትን የማስፈን ስራ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። የኮሚሽኑን የአሰራር ስርዓት ከማሻሻልና ብቃት ከማሳደግ አኳያ በተሰሩ ስራዎች ሶስት የተለያዩ ሕጎችን በማዘጋጀት ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉን ኮሚሽነሩ አስረድተዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም ተግባራቱን ይበልጥ አጠናክሮ በማስቀጠል የተመዘገቡ ሀብቶችን ትክክለኛነት ማጣራትና የሀብት ምዝገባን በቴክኖሎጂ የማስደገፍ ስራ በትኩረት ይሰራል ብለዋል ።
በዞኑ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ16 ሺህ በላይ የተለያዩ የታዳሽ ሃይል አማራጮች ለማህበረሰቡ እንዲቀርቡ ተደርጓል
Jul 11, 2025 43
ወልዲያ ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፡- በሰሜን ወሎ ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ16 ሺህ በላይ የተለያዩ የታዳሽ ሃይል አማራጮችን በማቅረብ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የዞኑ ውሃና ኢነርጂ መምሪያ አስታወቀ። በመምሪያው የአማራጭ ኢነርጂ ቡድን መሪ ወይዘሮ ትርሃስ እቋር ለኢዜአ እንደገለጹት በገጠር ተበታትኖ የሚኖረውን ማህበረሰብ በታዳሽ ሃይል ተጠቃሚ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ ነው። በበጀት ዓመቱ ከ16 ሺህ በላይ የታዳሽ ሃይል አማራጮችን በማቅረብ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን ገልጸዋል። ከቀረቡት የሃይል አማራጮች ውስጥም 12 ሺህ 187 የተሻሻሉ ማገዶ ቆጣቢ ምድጃዎች፣ 3 ሺህ 764 የሶላር ቁሳቁሶችና 112 የባዮ ጋዝ ግንባታ መሆናቸውን አስረድተዋል። በቀረቡት የሃይል አማራጮችም 16 ሺህ 63 እማና አባዎራዎችን ከነሙሉ ቤተሰቦቻቸው ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። የሃይል አማራጮቹን ማቅረብ የተቻለውም ከመንግስትና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች በተገኘ ከ15 ነጥብ 6 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪና በህብረተሰቡ ተሳትፎ መሆኑን አስገንዝበዋል። በመቄት ወረዳ የ017 ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶ አደር አስረሴ ቦጋለ እንደገለጹት ከባለሙያዎች በተሰጣቸው ምክር በመታገዝ የባዮ ጋዝ ግንባታ በማካሄድ ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል። በዚህም የምግብ ማብሰል፣ የመብራት አገልግሎት፣ ከባዮ ጋዝ ተረፈ ምርቱ የተፈጥሮ ማዳበሪያና ሌሎች ጥቅሞችን ማግኘታቸውን ተናግረዋል። "የተሻሻለ ፈጣን የምድጃ ተጠቃሚ በመሆናቸው ከኩበትና ከእንጨት ጪስ ስቃይ መገላገላቸውን የገለጹት ደግሞ በዞኑ የላስታ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ወይዘሮ እታለም ጎሹ ናቸው። " በማገዶ ፍለጋ ብዙ ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን ያባክኑ እንደነበር ጠቁመው አሁን ላይ ጤናቸውን በጠበቀና ወጪን በቀነሰ መልኩ ምግብ አብስለው ቤተሰባቸውን እየመገቡ መሆኑን ተናግረዋል።
በመዲናዋ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ 15 ሺህ 960 ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቅተዋል
Jul 11, 2025 67
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ) ፡- በመዲናዋ በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት 15 ሺህ 960 ፕሮጀክቶች በመንግሥትና በህብረተሰብ ተሳትፎ ተጠናቀው ለአገልግሎት መብቃታቸውን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። 3ኛው የአዲስ አበባ ምክር ቤት 4ኛ አመት የስራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ጉባኤ መካሄድ ጀምሯል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ የ2017 በጀት ዓመት የዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት በማቅረብ ላይ ይገኛሉ። በሪፖርታቸውም በ2017 በጀት ዓመት የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በርካታ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። ከእነዚህም መካከል የአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል፣ የገበያ ማዕከላት፣ የጤና የትምህርት የኪነጥበብ እና ሌሎችም መሰረተ ልማቶች ተጠቃሽ ናቸው ብለዋል። የአቅመ ደካማ ቤቶችን መገንባት እና ማደስ በበጎ ፈቃደኞች ብቻ የተሰራው 8 ሺህ 786 ቤቶች ሲሆን በከተማ አስተዳደሩ በጀት የተገነቡ መኖሪያ ቤቶች ደግሞ 5 ሺህ 176 መኖሪያ ቤቶች ናቸው ብለዋል። በኮሪደር ልማቱም በካዛንችስ፣ ቦሌ፣ ልደታ፣ ላፍቶ፣ አራት ኪሎ እና ሌሎችም በግልና በመንግስት ተሳትፎ 5 ሺህ 563 ሱቆች መጠናቀቃቸውን ያነሱት ከንቲባዋ፥ 1 ሺህ 64 መስሪያ ሼዶችም ወደ አገልግሎት ገብተዋል ነው ያሉት። በቀዳማዊ ልጅነት ንቅናቄም አዲስ አበባ ህጻናትን ለማሳደግ ምቹ ከተማ እንድትሆን በተጀመሩ ተግባራት 1 ሺህ 155 የህጻናት መጫወቻዎች መገንባታቸውን ገልጸዋል። ለወጣቶች ስፖርት ማዘውተሪያ 122 ሜዳዎች ተጠናቀው ወደ አገልግሎት መግባታቸውንም አብራርተዋል። በበጀት ዓመቱ በመጀመሪያው ምዕራፍ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ 153 የመኪና ማቆሚያና ተርሚናሎች ተጠናቀው ወደ አገልግሎት መግባታቸውን ገልጸዋል። ሌሎችም በርካታ የልማት ሥራዎችን ጨምሮ 15 ሺህ 960 ፕሮጀክቶች ተገንብተው ለአገለግሎት መብቃታቸውን በማንሳት ከእነዚህ ውስጥም 16ቱ ሜጋ ፕሮጀክቶች ናቸው ብለዋል። ከዚህም ባለፈ 9 ሺህ የሚሆኑት በህብረተሰብ ተሳትፎ እና በበጎ ፈቃድ አገልግሎት የተሰሩ መሆናቸውን አንስተዋል። የከተማዋን የመንገድ ተደራሽነትና የትራፊክ ፍሰትን የሚያሻሽሉ ጥራት ያላቸው የመንገድ መሰረተ ልማቶችን ለመገንባት በተሰራው ስራም 1 ሺህ 392 ኪሎ ሜትር የአስፋልት፣ የኮብል፣ የጠጠር፣ እና የእግረኛ መንገዶች ግንባታና ጥገና መከናወኑን ጠቅሰዋል።
የክልሉ መንግስት የጤና አገልግሎት ለሕብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ ተጠቃሚነቱን የሚያጎለብት ተግባር እያከናወነ ነው
Jul 10, 2025 86
ቦንጋ ፤ ሐምሌ 3/2017 (ኢዜአ)፡- የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል መንግስት የጤና አገልግሎት ለሕብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ ተጠቃሚነቱን ይበልጥ የሚያጎለብት ተግባር እያከናወነ መሆኑ ተገለጸ። የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) በካፋ ዞን የተገነባውን የቆንዳ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል መርቀው ሥራ አስጀምረዋል። በተጨማሪም በካፋ ዞን ሳይለም ወረዳ ከ78 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የተደረገባቸው የያዶታ ኮንስትራክሽንና ኢንዱስትሪያል ኮሌጅና የያዶታ ጤና ጣቢያ ቀዶ ጥገና ማዕከልንም መርቀዋል ። በዚህ ወቅት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት፤ የክልሉ መንግስት የዜጎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን የሚያሳድጉ በርካታ ተግባራት እያከናወነ ነው ። በተለይም ከማህበራዊ ዘርፍ ውስጥ የጤና አገልግሎት ተደራሽነትንና ጥራቱን ለማሻሻል በተወሰደው እርምጃ የዛሬውን ጨምሮ ባለፉት የለውጥ ዓመታት አራት የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታሎች ተመርቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ ተደርጓል ብለዋል። በተጨማሪም በርካታ የማስፋፊያና በግብአት የማሟላት ስራም መከናወኑን አንስተዋል። ዛሬ የተመረቀው የቆንዳ ሆስፒታል ለወረዳውና ለአጎራባች አካባቢዎች ነዋሪዎች አገልግሎት የሚሰጥ ነው ያሉት ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ፤ የክልሉ መንግስት የጤና አገልግሎት ለሕብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ ተጠቃሚነቱን ይበልጥ የማጎልበት ተግባር እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። የክልሉ ጤና ቢሮ ሀላፊ አቶ ኢብራሂም ተማም በበኩላቸው፤ የቆንዳ የመጀመሪያ ሆስፒታል በክልሉ መንግስት 120 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መገንባቱን ገልጸዋል። የሆስፒታሉ መገንባት ሕብረተሰቡ የተሻለ የጤና አገልግሎት እንዲያገኝ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል። ዛሬ የተመረቀው የቆንዳ ሆስፒታል በሕብረተሰቡ ሲነሳ ለቆየው ጥያቄ መልስ የሰጠ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ ናቸው ። በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደርና የግብርና ቢሮ ሀላፊ አቶ ማስረሻ በላቸውን ጨምሮ ሌሎችም ከፍተኛ አመራሮችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
በክልሉ በጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች የበርካቶችን ሕይወት እየታደጉ ነው
Jul 10, 2025 71
ወላይታ ሶዶ፤ሐምሌ 3/2017 (ኢዜአ))፡-በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በጎ ፈቃደኛች በተከታታይ እያበረከቱት ያለው የደም ልገሳ የበርካቶችን ሕይወት እየታደጉ መሆኑ ተገለጸ። የክልሉ ጤና ቢሮ የዓለም የደም ለጋሾ ቀንን ምክንያት በማድረግ ለበጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾችና ተቋማት የምስጋና እና የእውቅና መርሃ ግብር ዛሬ በወላይታ ሶዶ ከተማ አካሂዷል። ዕውቅና ከተሰጣቸው በጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች መካከል ወጣት ሄኖክ ኮይራ በአርአያነት ተጠቅሷል። ወጣቱ በአርአያነት የተጠቀሰውም ለ65 ተከታታይ ጊዜ በበጎ ፈቃደኝነት ደም በመለገሱ ሲሆን፤ለዚህም ከክልሉ ጤና ቢሮ የዕውቅናና ምስጋና የምስክር ወረቀት እንዲሁም ሜዳሊያ ተበርክቶለታል። ወጣት ሄኖክ የሚለገሰው ደም በተለያዩ ምክንያቶች ደም የሚያስፈልጋቸውን ሰዎች ሕይወት እየታደገ መሆኑን ሲያስብ እና ሲመለከት የአዕምሮ እርካታ ከመስጠት ባለፈ ደስታ እንደሚሰማው ይናገራል። የክልሉ ጤና ቢሮ ለተከታታይ 65 ጊዜ ደም በመለገሱ የሰጠው እውቅና ልግስናውን ይበልጥ ለማጠናከር የሚያበረታታው መሆኑን ገልጿል። ሌሎችም ወጣቶች የሚተካ ደም በመለገስ የማይተካ የሰው ሕይወት ቢታደጉ በህይወታቸው ይበልጥ ደስተኛ ሊሆኑ እንደሚችሉ አስተያየት ሰጥቷል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ ሃላፊ አቶ እንዳሻው ሽብሩ በበኩላቸው፤ ወጣት ሄኖክ ኮይራን ጨምሮ በበጎ ፈቃድ ደም የሚለግሱ አካላት የበርካቶችን ሕይወት እየታደጉ በመሆናቸው ሊመሰገኑ ይገባል ብለዋል። ቢሮው የሕብረተሰቡን ግንዛቤ ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት የለጋሾች ቁጥር እየጨመረ መሆኑን ተናግረዋል። በበጎ ፈቃድ ደም በመለገስ አስተዋጽኦ የሚያደርጉ አካላትን ዕውቅና የመስጠት ስራ አጠናክረው እንደሚቀጥሉም ሃላፊው አስታውቀዋል።
በኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግርን ለማሳካት የሁሉም ሚና ወሳኝ ነው
Jul 10, 2025 76
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ ዘላቂ እና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግርን ለማሳካት የሁሉም አካላት ሚና ወሳኝ መሆኑ ተገለጸ፡፡ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "ከራዕይ ወደ ተግባር፤ የኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ" በሚል መሪ ሀሳብ በኢትዮጵያ ሥርዓተ ምግብ ላይ ያደረገ ውይይት ተካሂዷል። በዚሁ ወቅት የመነሻ ጽሁፍ ያቀረቡት የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬው ተገኝ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለዘላቂ የልማት ግቦች ስኬት የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ትገኛለች። ኢትዮጵያ የምግብ ስርዓት ሽግግር ትግበራን በመጀመር ግንባር ቀደም ሀገር መሆኗን ገልጸዋል። 2ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ በኢትዮጵያ እና በጣሊያን አስተናጋጅነት ከሐምሌ 20 እስከ 22 ቀን 2017 በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ገልጸዋል። ጉባዔው በኢትዮጵያ መካሄዱ ለሀገር ገጽታ ግንባታ ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም ኢትዮጵያ ለጀመረችው የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ እውቅና የሚሰጥ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በተለይም ከለውጡ ወዲህ የምግብ ስርዓት ሽግግርን የሚያፋጥኑ የተለያዩ ብሔራዊ ፕሮግራሞችን በመቅረጽ በትኩረት እየሰራች እንደምትገኝ ይታወቃል። ለአብነትም የሌማት ትሩፋት፣ የስንዴ ልማት፣ አረንጓዴ አሻራ፣ የትምህርት ቤት ምገባ፣ ኢትዮጵያ ታምርት እንዲሁም የሰቆጣ ቃል-ኪዳን ኢንሼቲቮች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ የትምህርት ቤቶች ምገባ ኢኒሼቲቭ ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬዓለም ሺባባው በመድረኩ የኢትዮጵያ መንግስት የሰቆጣ ቃልኪዳን እና የተማሪ ምገባ ኢኒሼቲቮችን በመውሰድ ለትውልድ ግንባታ ትልቅ ሥራ እየሰራ መሆኑን አንስተዋል፡፡ በዚህም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ብቻ ከ8 መቶ ሺህ በላይ ተማሪዎች በቀን ሁለት ጊዜ በመመገብ ላይ መሆኑን ተናግረው፤ በሰቆጣ ቃልኪዳንም ለትውልድ ግንባታ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የተፈጥሮ ሳይንስና ስነ ቀመር ኮሌጅ ዲን ቢቂላ ወርቅነህ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ የኢትዮጵያ ግብርና ምርታማነት አቅምን ማሳደግ የሁሉም ሚና ነው ብለዋል፡፡ በተለይም የግሉ ሴክተር የሚጠበቅበትን መወጣት እንዳለበት አንስተው ወደ ምግብ ማቀነባበር እንዲሁም እሴትን የመጨመር ስራ መስራት እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡ የኤንቢሲ ቴሌቪዥን ዋና ስራ አስፈጻሚ ብሩክ ከበደ፤ የምግብ ስርዓት እና የምግብ ሉዓላዊነት የመገናኛ ብዙሃን ዋነኛው አጀንዳ ነው ብለዋል፡፡ በተጨማሪም መገናኛ ብዙሃን በሀገራዊ ዋና ዋና ጉዳዮች ዙሪያ በርካታ ስራዎች መስራታቸውን ጠቁመው፤ ለአብነትም የአረንጓዴ አሻራ፣ የሌማት ትሩፋት እንዲሁም በግብርና መካናይዜሽን ዙሪያ በርካታ ስራዎች መሥራታቸውን ጠቁመዋል፡፡ የኒው ላይፋ ቴን ቻሌንጅ ዴቬሎፕመንት ኤክስኪዩቲቭ ዳይሬክተር ሔለን ጥላሁን በበኩላቸው የምግብ ስርዓትን አሻጋሪና አካታች ለማድረግ ወጣቶችን፣ ሴቶችን እና አካል ጉዳተኞችን አሳታፊ ማድረግ እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡ በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት የሚካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የምግብ ስርዓት ጉባዔን በስኬት ለማስተናገድ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ፡፡
የተጀመሩ የሰላምና የልማት ተግባራትን ለማጠናከር በትኩረት እየተሰራ ነው
Jul 10, 2025 72
ገንዳ ውሃ ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ የተጀመሩ የሰላምና የልማት ተግባራትን በማጠናከር የህዝቡን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የምዕራብ ጎንደር ዞን አስተዳደር አስታወቀ። በዞኑ ባለፈው በጀት ዓመት የተሰሩ የሰላምና ልማት ስራዎችን የሚገመግምና በቀጣይ ስለሚሰሩ ተግባራት አቅጣጫ የሚያስቀምጥ መድረክ በገንዳ ውኃ ከተማ ተካሄዷል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ እያሱ ይላቅ እንዳሉት የዞኑን ፀጋ አሟጦ በመጠቀም የህዝቡን የሰላምና ልማትና ስራዎች ተጠቃሚ ለማድረግ በቁርጠኝነት እየተሰራ ነው። በአካባቢያቸው ያጋጠመን የጸጥታ ችግሮች ከመፍታት ጎን ለጎን ልማትን ለማፋጠንና የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት መሰራቱን አውስተዋል። ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን በተካሄደው ጥረትም የዞኑ ህዝብ የነቃ ተሳትፎ አሁን በዞኑ ለሰፈነው ሰላም ሚና መጫወቱንም አስረድተዋል። የዞኑ ትምህርት መምሪያ ኃላፊ ደሳለኝ አያና በበኩላቸው በችግር ውስጥ ሆነው ተማሪዎችን ተቀብለው ያስተማሩ ትምህርት ቤቶችን በማጠናከርና በቀጣይ ያልጀመሩትን ለማስጀመር በቁርጠኝነት ይሰራል ብለዋል። በዞኑ የትምህርት ገፅታን ለማሻሻልና የትምህርት ጥራትን ለማሳደግ ከህብረተሰብ ተሳትፎና ከአጋር አካላት ጋር በቅንጅት እየተሰራ እንደሚገኝም አብራርተዋል። ባለፈው ዓመት በርካታ የህዝብ ለህዝብ ውይይቶች ተደርገው የህዝቡን ሰላምና ልማት የማረጋገጥ ተግባር መከናወኑን የገለፁት ደግሞ በብልፅግና ፓርቲ የዞኑ ፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ ወይዘሮ ደመቅ አበበው ናቸው። በዞኑ አብዛኞቹ ቀበሌዎች ወደ ሰላም መመለስ መቻላቸውን አስረድተው ሰላምን በዘላቂነት በማፅናት የፀጥታና የልማት ሰራዎች በተጠናከረ ሁኔታ እንደሚሰሩም አመልክተዋል። የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ምክትል ኃላፊ አየለ አናውጤ (ዶ/ር) እንዳሉት በክረምት ወቅት ከመደበኛ ስራዎች ጎን ለጎን የበጎ ፈቃድ አገልግሎትን ማሳለጥ እንደሚገባ ጠቁመዋል። የዞኑን አንፃራዊ ሰላም ወደ ተሟላ ሰላም ለማሸጋገር የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች መመለስ እንደሚገባም አፅንኦት ሰጥተዋል። ከግምገማ መድረኩ ጎን ለጎንም የደም ልገሳ መርሃ ግብር ተካሄዷል።
ሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ እንዲሳካ ወጣቶች የሚያደርጉትን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ድጋፍ ማጠናከር አለባቸው
Jul 10, 2025 52
አርባ ምንጭ ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ሀገራዊ የብልጽግና ጉዞ እንዲሳካ ወጣቶች አቅማቸውን በማስተባበር የሚያደርጉትን ሁለንተናዊ ተሳትፎና ድጋፍ ማጠናከር እንዳለባቸው የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታወቀ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ምክር ቤት ምስረታ ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የወጣቶች ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ወይዘሮ የሺወርቅ አያና እንደገለጹት ወጣቶች ባለራዕይ በመሆን ባላቸው እውቀትና ክህሎት ለሀገር የብልጽግና ጉዞ መሳካት የበኩላቸውን ሊወጡ ይገባል። ለሀገር ሰላምና ልማት መጠናከር የወጣቶች የነቃ ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑን ገልጸው፣ መንግስት ለወጣቱ የሰጠውን ልዩ ትኩረት በመጠቀም በሁሉም የልማት መስኮች የሚያደርጉትን ተሳትፎና ያላቸውን ተጠቃሚነት ሊያሳድጉ ይገባል ብለዋል። መንግስት የወጣቶችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሲያከናውናቸው የነበሩ ተግባራትን በቀጣይም አጠናክሮ እንደሚቀጥል ወይዘሮ የሺወርቅ ጠቁመዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ወጣቶችና ስፖርት ቢሮ ምክትልና የወጣቶች ዘርፍ ሃላፊ አቶ ማርቆስ ማቴዎስ በበኩላቸው እንዳሉት ቢሮው የወጣቶችን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራ ይገኛል። የክልሉ የወጣቶች ምክር ቤት አስፈጻሚ አካላት ምርጫ ብዝሃነትን መሠረት ያደረገ፣ ዴሞክራሲያዊና ፍትሃዊ መሆኑንም ገልጸዋል። ተመራጮች የክልሉን ወጣቶች ወክለው በተለያዩ መድረኮች እንደሚሳተፉ ገልጸው፣ በቀጣይ እንቅስቃሴያቸው ምክንያታዊ በመሆን ለወጣቶች ሁለንተናዊ ድምፅ ሊሆኑ ይገባል ሲሉም አሳስበዋል። የክልሉ ብሎም የሀገሪቱ እድገትና ሰላም በዘላቂነት ተጠናክሮ እንዲቀጥልም ወጣቶች የበኩላቸውን እንዲወጡ አቶ ማርቆስ ጥሪ አቅርበዋል። የክልሉ ወጣቶች ምክር ቤት ፕሬዚዳንት ሆኖ የተመረጠው ወጣት ቲቶ ሐኩቴ በበኩሉ፣ በቀጣይ የወጣቶች ሁለንተናዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት እንዲጎለብትና የወጣቱ ጥያቄዎች በሂደት እንዲመለሱ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅርበት እንደሚሰራ ተናግሯል። የክልሉ ወጣቶች ያላቸውን እውቀትና ጉልበት አቀናጅተው ለክልሉና ለሀገር ልማት በማዋል የበኩላቸውን እንዲወጡም አስገንዝቧል። ዛሬ በተካሄደው የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የወጣቶች ምክር ቤት ምስረታ ላይ በሥራ አስፈጻሚነት የተመረጡ 15 ወጣቶችም ቃለ መሃላ ፈጽመዋል።
ደምና የዓይን ብሌንን በመለገስ የሰዎችን ህይወት ከመታደግ ባለፈ ፍቅርና ወንድማማችነትን ማጎልበት ይገባል
Jul 10, 2025 59
ወላይታ ሶዶ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ ደም እና የዓይን ብሌንን በመለገስ የሰውን ህይወት ከመታደግ ባለፈ ፍቅርና ወንድማማችነትን ለማጎልበት መስራት እንደሚገባ ተገለጸ። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ጤና ቢሮ 21ኛውን ዓለም አቀፍ የደም ለጋሾ ቀንን በማስመልከት ለበጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾችና ተቋማት የምስጋና እና የእውቅና መርሃ ግብር አካሂዷል። በመድረኩ የተገኙት በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የወላይታ ሶዶ ክላስተር አስተባባሪ እና የክልሉ ፋይናንስ ቢሮ ኃላፊ ተፈሪ አባተ በክልሉ የደም አቅርቦቱን ለማሳደግ እየተሰራ ነው። በተለያዩ ምክንያቶች ደም የሚያስፈልጋቸውን ወገኖች ለመታደግ የተጀመረው ደም የማሰባሰብ ሥራ አበረታች ውጤት እየተገኘበት መሆኑን ጠቁመዋል። የደም እና የዓይን ብሌን ልገሳ ውድ ስጦታ መሆናቸውን ገልጸው፣ ለጋሾችም የህይወት ዘመን አምባሳደሮች በመሆናቸው ክብር ይገባቸዋል ብለዋል። ከክልሉ ህዝብ ቁጥር ጋር ሲታይ ከህብረተሰቡ የሚሰበሰበው ደም በቂ እንዳልሆነ ጠቁመው በቀጣይ የደም ለጋሾችን ቁጥር ለማሳደግ በቅንጅት የሚደረገው ጥረት ይጠናከራል ነው ያሉት። የኢትዮጵያ የደም እና ህብረ ህዋስ ባንክ አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ወይዘሮ ጤናዬ ደምሴ በበኩላቸው የደም ልገሳ መርሃ ግብር የደም ለጋሾችን ቁጥር እያሳደገ ቢመጣም ከሚያስፈልው ደም አንፃር በቂ ስላልሆነ አጠናክሮ መቀጠል ይገባል ብለዋል። በደም ህዋስ የሰዎችን ህይወት ከመታደግ በተጨማሪ መድኃኒት ለማምረት የ5 ዓመት ዕቅድ ተይዞ እየተሰራ መሆኑንም ምክትል ዳይሬክተሯ ጠቁመዋል። ይህም ከውጭ ሀገር በውድ ዋጋ የሚገባን መድኃኒት በሀገር ውስጥ ለማግኘት ከማስቻሉ ባለፈ የውጭ ምንዛሬን እንደሚያስቀርም አስረድተዋል። በሀገር ውስጥ ለሚገኙ 55 የደም ባንኮች አስፈላጊው ድጋፍ እና ክትትል እየተደረገ መሆኑን ጠቁመው ህብረተሰቡም ደም መለገስን ባህሉ በማድረግ የሌሎችን ህይወት መታደግና የህይወት ግዴታውን መወጣት ይኖርበታል ብለዋል። መድረኩ ለበጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾችና ተቋማት ምስጋናና እውቅና ከመስጠት ባለፈ አዳዲስ ደም ለጋሾችን የማፍራት ዓላማ እንዳለው ተመላክቷል። በመርሃ ግብሩ ከክልል አስከ ዞን ያሉ አመራሮች፣ በጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች፣ የተቋማት ተወካዮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።
በበጀት ዓመቱ ከበጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች ከ423 ሺህ በላይ ዩኒት ደም ተሰብስቧል - አገልግሎቱ
Jul 10, 2025 51
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በተጠናቀቀው የ2017 በጀት ዓመት ከበጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሾች ከ423 ሺህ በላይ ዩኒት ደም መሰብሰቡን የኢትዮጵያ ደምና ሕብረ ሕዋስ ባንክ አገልግሎት አስታወቀ፡፡ ባንኩ በሁለት ወር የክረምት የበጎ ፈቃድ ደም ልገሳ መርሃ-ግብር 70ሺህ ዩኒት ደም ለመሰብሰብ ማቀዱንም ገልጿል፡፡ የአገልግሎቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ሃብታሙ ታዬ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በአዲስ አበባና በክልሎች የደም ልገሳ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎች በስፋት ተከናውኗል። በትምህርት ቤቶች የደም ልገሳ ክበቦችን በማቋቋም የተማሪዎችን ግንዛቤ የማሳደግ ሥራ በትኩረት መሰራቱንም እንዲሁ። የግንዛቤ ፈጠራ ስራውን ተከትሎ ከጊዜ ወደ ጊዜ ስለ ደም ልገሳ ያለው አመለካከት ለውጥ እየታየበት እንደሚገኝ አስታውቀዋል፡፡ በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከ423ሺህ በላይ ዩኒት ደም መሰብሰብ መቻሉን ገልጸዋል፡፡ ይህም ከጊዜ ወደ ጊዜ በበጎ ፍቃደኝነት ደም ለመለገስ የሚመጡ ስዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን የሚያሳይ መሆኑን አመላክተዋል። ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አክለውም በሁለት ወራት የክረምት የበጎ ፈቃድ ደም ልገሳ መርሃ-ግብር 70ሺህ ዩኒት ደም ለመሰብሰብ መታቀዱንና በቂ ዝግጅት መደረጉን አንስተዋል። የደም ልገሳ ተግባር የሰዎችን በተለይም የእናቶችን ህይወት መታደግ በመሆኑ ህብረተሰቡ ደም መለገስን ባህል በማድረግ ህይወት እንዲታደግ ጥሪ አቅርበዋል። በጎ ፈቃደኛ ደም ለጋሽ የሆኑት ወይዘሮ አሰጋሽ ጎሳ ለ121ኛ ጊዜ ደም መለገሳቸውን ጠቁመው፤ በዚህም ህይወት እየታደጉ በመሆኑ የሕሊና እርካታ እንደሚሰማቸው አመልክተዋል። በአሁኑ ሰዓት በማኅበረሰቡ ዘንድ ያለው ደም የመለገስ ልምድ እየዳበረ መምጣቱን የተናገሩት ደግሞ ለ81ኛ ጊዜ በበጎ ፈቃድ ደም መለገሳቸውን የገለጹልን አቶ ሞገስ በዳኔ ናቸው፡ ማንኛውም ሰው በደም እጦት ምክንያት እንዳይጎዳ በጎፈቃደኛ ለጋሾች ደም እንዲለግሱ ጥሪ አቅርበዋል።
በአዲስ አበባ የሚካሄደው የተመድ የስርዓተ ምግብ ጉባኤ ኢትዮጵያ በምግብ ስርዓት ላከናወነችው ሥራ እውቅና የሚሰጥ ነው
Jul 10, 2025 139
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የሚካሄደው የተመድ የስርዓተ ምግብ ጉባኤ ኢትዮጵያ በምግብ ስርዓት ላከናወነችው ሥራ እውቅና የሚሰጥ መሆኑን የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬው ተገኝ(ዶ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ከኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር "ከራዕይ ወደ ተግባር፤ የኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ" በሚል መሪ ሐሳብ ዐበይት ትኩረቱን በኢትዮጵያ ሥርዓተ ምግብ ላይ ያደረገ ውይይት በማካሄድ ላይ ይገኛል። በዚሁ ወቅት የመነሻ ጽሁፍ ያቀረቡት የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ፍሬው ተገኝ(ዶ/ር) እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለዘላቂ የልማት ግቦች ስኬት የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ትገኛለች። ኢትዮጵያ የምግብ ስርዓት ሽግግር ትግበራን በመጀመር ግንባር ቀደም ሀገር መሆኗን ገልጸዋል። በዚህም የተለያዩ የልማት ኢኒሼቲቮች መተግበራቸውን ጠቁመው፤ የሌማት ትሩፋት፣ የስንዴ ልማት፣ የአረንጓዴ አሻራ እና ሌሎችን ለአብነት አንስተዋል። 2ኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ ከሐምሌ 20 እስከ 22 ቀን 2017 በአዲስ አበባ በኢትዮጵያ እና በጣሊያን አስተናጋጅነት እንደሚካሄድ ገልጸዋል። ጉባዔው በኢትዮጵያ መካሄዱ ለሀገር ገጽታ ግንባታ ትልቅ ፋይዳ ያለው መሆኑን ገልጸው፤ በተለይም ኢትዮጵያ ለጀመረችው የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ እውቅና የሚሰጥ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በተለይም ከለውጡ ወዲህ የምግብ ስርዓት ሽግግርን የሚያፋጥኑ የተለያዩ ብሔራዊ ፕሮግራሞችን በመቅረጽ በትኩረት እየሰራች እንደምትገኝ ይታወቃል። ለአብነትም የሌማት ትሩፋት፣ የስንዴ ልማት፣ አረንጓዴ አሻራ፣ የትምህርት ቤት ምገባ፣ ኢትዮጵያ ታምርት እንዲሁም የሰቆጣ ቃል-ኪዳን ኢንሼቲቮች ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት የሚካሄደው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የምግብ ስርዓት ጉባዔን በስኬት ለማስተናገድ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች እየተከናወኑ ይገኛሉ፡፡
ሰራዊቱ የሀገር ሉዓላዊነትን ከማስከበሩ በተጓዳኝ ማህበራዊ አገልግሎቶች ላይ እየተሳተፈ አጋርነቱን አጠናክሮ ቀጥሏል
Jul 10, 2025 61
ጅማ ፤ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፡- ሰራዊቱ የሀገር ሉዓላዊነትን ከማስከበር መደበኛ ስራው በተጓዳኝ ማህበራዊ አገልግሎቶች ላይ በንቃት እየተሳተፈ አጋርነቱን አጠናክሮ መቀጠሉን የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ዘውዱ በላይ ገለጹ። የዳሎል ማእከላዊ ዕዝ ሰራዊት አባላት ባለፉት አስር ቀናት ሲያካሄዱ የቆዩት ስፖርት ፌስቲቫል ውድድር ማጠቃለያ እና ደም ልገሳ መርሃ ግብር ዛሬ አካሄደዋል። በዚህ ወቅት የዳሎል ማዕከላዊ እዝ ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ዘውዱ በላይ፤ ሰራዊቱ የሀገር ሉዓላዊነትን የማስከበር መደበኛ ስራውን በብቃት እየፈጸም በጀግንነት መቀጠሉን ተናግረዋል። በተጓዳኝም በማህበራዊ አገልግሎቶች ላይ በንቃት በመሳተፍ አጋርነቱን እያጠናከረ መቀጠሉን ገልጸው፤ የዕዙ አባላት በዚህ ረገድ አበረታች እንቅስቃሴ እያደረጉ መሆኑን አስታውቀዋል። የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝም ተልዕኮን ለመፈጸም በተሻለ ዝግጁነት ላይ እንደሚገኝ ያመለከቱት ዋና አዛዡ፤ በቀጣይም በአካላዊ ብቃትና ስነ ልቦናዊ ዝግጅነቱ ይበልጥ እንደሚጠናከር አስረድተዋል። ዛሬ የተጠናቀቀው የስፖርት ፌስቲቫልም ሰራዊትና ስፖርት የማይለያዩ ተግባራት መሆኑን ተረድተው ለውድድሩ መሳካት አስተዋጽኦ ያበረከቱ አካላት ሊመሰገኑ ይገባል ብለዋል። የዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ኮሎኔል በዛብህ ይመር በበኩላቸው፤ የሰራዊቱን ብቃት ይበልጥ ለማጎልበት ያለመ የስፖርት ውድድር መካሄዱን ተናግረዋል። በዕዙ ስር የሚገኙ ኮሮች በስፖርታዊ ውድድሩ መሳተፋቸውን አንስተው፤ ውድድሩም የተሳካ መሆኑን ጠቁመዋል። የጅማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ጠሃ ቀመር በወቅቱ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ዳሎል ማዕከላዊ ዕዝ በአካባቢው ሰላም ፀንቶ እንዲቀጥል የማይተካ ሚና እየተወጣ ነው ብለዋል። የዕዙ ስራ የበለጠ እንዲቃና አስተዳደሩ የሚጠበቅበትን ድጋፍ ሁሉ እንደሚያደርግም አረጋግጠዋል። በመዝጊያ መርሃ ግብሩ ላይ የሰራዊቱ ከፍተኛ መኮንኖች፣ የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዚዳንት አቶ ዛዲግ አብረሃ፣ የጅማ ዞን አስተዳደሪ አቶ ቲጃኒ ናስር እና ሌሎችም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።
መገናኛ ብዙሃን ኢትዮጵያ የምታስተናግደውን ሁለተኛ የተመድ የስርዓተ ምግብ ጉባኤ በሚገባ ማስተዋወቅ አለባቸው- ማንደፍሮ ንጉሴ(ዶ/ር)
Jul 10, 2025 75
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ መገናኛ ብዙሃን ኢትዮጵያ የምታስተናግደውን ሁለተኛ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ አስቀድመው ማስተዋወቅ እንደሚገባቸው የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ(ዶ/ር) አስገነዘቡ። ሁለተኛው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስርዓተ ምግብ ጉባኤ ከሐምሌ 20 እስከ 22 ቀን 2017 ዓ.ም በኢትዮጵያ እና ጣልያን የጋራ አዘጋጅነት ይካሄዳል። በጉባኤው ላይ የ160 ሀገራት ተወካዮች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል። የምግብ ስርዓት ትራንስፎርሜሽን ኢንቨስትመንት እና ፋይናንስ፣ የምግብ ስርዓት ሽግግር ሁለንተናዊነት እና የተገቡ ቃሎችን ከመፈጸም አንጻር ያለውን የተጠያቂነት ስርዓት ማጠናከር ጉባኤው ትኩረት የሚያደርግባቸው ሀሳቦች ናቸው። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት እና የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት “ከራዕይ ወደ ተግባር: የኢትዮጵያ ዘላቂና አካታች የምግብ ስርዓት ሽግግር ጉዞ” በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጁት የፓናል ውይይት እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ(ዶ/ር)፣ የኢትዮጵያ ግብርና ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወንዳለ ሀብታሙ፣ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰይፈ ደርቤ እና ሌሎች እንግዶች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ ግብርና ትራንስፎርሜሽን ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ማንደፍሮ ንጉሴ(ዶ/ር) የምግብ ዋስትና በግለሰብ፣ በማህበረሰብ እና በሀገር ደረጃ ማረጋገጥ ወሳኝ ነው ብለዋል። እንደ ሀገር የተያዘው ዋነኛ ግብ የምግብ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ መሆኑንም ጨምረው አመልክተዋል። የምግብ ሉዓላዊነት የምግብ አመራረታችንን በኛ ቁጥጥር ስር የማድረግ እና ዜጎችን በሌሎች ላይ ጥገኛ ሳንሆን በራሳችን መመገብ መቻል እንደሆነ ተናግረዋል። የምግብ ስርዓት ሽግግር የምግብ ሉዓላዊትን የያዘ ጉዳይ መሆኑን ጠቅሰው መንግስት በጉዳዩ ላይ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በምግብ ስርዓት ሽግግር ከምርት እስከ ተጠቃሚ ባለው ሰንሰለት ውስጥ ሁሉን አቀፍ ስራ እየተከናወነ መሆኑንም ዋና ዳይሬክተሩ ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለምግብ ስርዓት ሽግግር የአሰራር ማዕቀፎች በማዘጋጀት በመተግበሯ ውጤቶች ማስገኘታቸውን ጠቅሰዋል። ጤናማ ምግብ ለሁሉም ዜጎች ግብ ያለው የምግብ ስርዓት ሽግግር ላይ አመርቂ ውጤቶች መመዝገባቸውን ነው ያነሱት። ኢትዮጵያ በምግብ ስርዓት ሽግግር ያላትን ተሞክሮዎች በዓለም መድረኮች እያቀረበች እንደምትገኝም ገልጸዋል። ሁለተኛው የተመድ የስርዓተ ምግብ ጉባኤ በኢትዮጵያ መካሄዱ ሀገሪቱ ለምግብ ስርዓት ሽግግር ላከናወችው ስራ እውቅና የሰጠ ነው ብለዋል። መገናኛ ብዙሃንም ኢትዮጵያ የምታስተናግደውን ሁለተኛ የተመድ የስርዓተ ምግብ ጉባኤ አስቀድመው እንዲያስተዋውቁ ጥሪ አቅርበዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ስራ አስፈጻሚ ሰይፈ ደርቤ የኢትዮጵያ የብልፅግና ጉዞ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ ወሳኝ ነው ብለዋል። እንደ ሀገር ብሔራዊ ጥቅምን ለማስጠበቅ አምርቶ ራስን በመቻል አልፎም ለሌላው በመትረፍ የምግብ ሉዓላዊነትን በሁለንተናዊ ሁኔታ ማረጋገጥ ያለው ሚና ወሳኝ መሆኑንም አመልክተዋል። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ግብርናን ጨምሮ በተለያዩ ሀገራዊ አጀንዳዎች ላይ ትላልቅ የፓናል ውይይቶችን እያዘጋጀ መሆኑን አመልክተው የዛሬው ውይይትም ሀገራዊ ተልዕኮውን የመወጣት አካል ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በስርዓተ ምግብ ትራንስፎርሜሽን፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ እና በግብርናው ዘርፍ ባደረገቻቸው ሀገር በቀል ሪፎርሞች ያስመዘገበቻቸው ውጤቶች ጉባኤውን እንድታስተናግድ ለመመረጥ ምክንያቶች ናቸው። ኢትዮጵያ በስርዓተ ምግብ ለውጥ ውስጥ እየተወጣች ያለው የመሪነት ሚና እና በማደግ ላይ ከሚገኙ ሀገራት በስርዓተ ምግብ ተምሳሌት የሆነች ሀገር መሆኗ ተመድ ዓለም አቀፉን ከፍተኛ ጉባኤ በኢትዮጵያ እንዲያደርግ ቁልፍ ሚና ተጫውተዋል። በጉባኤው ኢትዮጵያ የስርዓተ ምግብ ሽግግርን ለማሳካት እያከናወነች ባለው ተግባር ዙሪያ ተሞክሮዋን ለዓለም ማህበረሰብ የማካፈል ስራ ታከናውናለች።