ማህበራዊ - ኢዜአ አማርኛ
ማህበራዊ
ብሔራዊ የስፔሻሊቲ ፕሮግራም በህክምና ዘርፍ ፍትሃዊ የባለሙያ ስርጭት እንዲኖር ያስችላል- ጤና ሚኒስቴር
Sep 29, 2023 125
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 18 /2016(ኢዜአ)፡-የስፔሻሊስት ሀኪሞችን ቁጥር ለማሳደግ የተጀመረው የስልጠና ፕሮግራም በአገር አቀፍ ደረጃ ፍትሃዊ የባለሙያዎች ስርጭት እንዲኖር የሚያስችል መሆኑን የጤና ሚኒስቴር ገለፀ። በሀገሪቱ የሚታየውን የህክምና ስፔሻሊቲ ባለሙያዎች እጥረት ለመፍታት የጤና ሚኒስቴር ከትምህርት ሚኒስቴርና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት ብሔራዊ የስፔሻሊቲ ፕሮግራም ጀምሯል። ፕሮግራሙ ከተጀመረ አራት ዓመታት ያስቆጠረ ሲሆን የስፔሻሊቲ ትምህርታቸውን የሚከታተሉ ሀኪሞች በማዕከል ደረጃ የሚመደቡበትና ፈተና የሚሰጥበት አሰራርንም ይከተላል። በጤና ሚኒስቴር የጤና ዘርፍ የሰው ሀብት ልማትና ማሻሻያ መሪ ስራ አስፈፃሚ አሰግድ ሳሙኤል እንዳሉት ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በጤና የሰው ኃይል ልማት ላይ በተሰራው ስራ በተለይ በቁጥር ደረጃ በርካታ መሻሻሎች እየታዩ ነው። ፕሮግራሙ ሲጀመር የህክምና ስፔሻሊቲ የሚሰጡ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት 8 እንደነበሩ አንስተው አሁን ላይ 19 ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በ22 የህክምና አይነቶች የስፔሻሊቲ ትምህርት እየሰጡ እንደሆነ ገልጸዋል። በዚህም በየዓመቱ ከ 1 ሺህ የማያንሱ የስፔሻሊቲ ሀኪሞች ተመርቀው ወደ ስራ እንደሚገቡ አስረድተዋል። የባለሙያዎች ምደባ በሚኒስቴሩ የሚካሄድ በመሆኑ በጤና ተቋማት ፍትሀዊ የሆነ ባለሙያዎች ስርጭት እንዲኖር ያስችላል ብለዋል። ፕሮግራሙ በሀገር ደረጃ የሚከናወኑ ከፍተኛ ንቀለ ተከላዎችን ለመስጠት የሚችሉ ብቃት ያላቸው ባለሙያዎችን ለማፍራት እንደሚያግዝም ጠቁመዋል፡፡ ሰልጠናዎቹን ከሚሰጡ ተቋማት መካከል የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሚሊኒየም ህክምና ኮሌጅ የትምህርት፣ ጥናትና ምርምር ምክትል ፕሮቮስት ዶክተር ሴና ዱጋሳ፤ ኮሌጁ በተለያዩ መርሃ ግብሮች 67 የህክምና ፕሮግራሞችን እየሰጠ እንደሚገኝ ጠቁመዋል ። ከእነዚህ መካከል 20 ዎቹ የስፔሻሊቲ 24ቱ ደግሞ የሰብስፔሻሊቲ መርሃግብሮች መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ኮሌጁ ፕሮግራሞቹን ሲቀርፅ የህብረተሰቡን የጤና ችግር በመለየት እንደሆነ አንስተዋል፡፡
በክልሉ የ2016 ዓ.ም የትምህርት ዘመን የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የሚያስችል ዝግጅት በማጠናቀቅ ወደ ተግባር ተገብቷል- ቢሮው
Sep 29, 2023 199
ቦንጋ ፤መስከረም 18/2016 (ኢዜአ) :-በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የ2016 የትምህርት ዘመን የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ የሚያስችል ዝግጅት በማጠናቀቅ ወደ ተግባር መገባቱን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ ። በክልሉ ለ2016 የትምህርት ዘመን የመማር ማስተማር ሥራ ውጤታማነት የመማሪያ ክፍሎች፣ የመምህራን መኖሪያ ቤቶች ግንባታና የተለያዩ ሥልጠናዎች ሲሰጡ መቆየታቸውም ተገልጿል። በክልሉ ትምህርት ቢሮ የመማር ማስተማር ዘርፍ ኃላፊና የቢሮው ምክትል ኃላፊ ዶክተር ደስታ ገነሜ፣ በ2016 ትምህርት ዘመን ከአንድ ሚሊዮን በላይ ተማሪዎችን ተቀብሎ ለማስተማር ታቅዶ ምዝገባ ሲከናወን መቆየቱን አስታውሰዋል። በዚህም ከነሐሴ 23/2015 ዓ.ም እስከ መስከረም 13/2016 ዓም ድረስ ከቅድመ አንደኛ እስከ 12ኛ ክፍል ድረስ የተማሪዎች ምዝገባ ስርዓት በተሳካ ሁኔታ ሲከናወን መቆየቱን ተናግረዋል። የመማር ማስተማር ሥራው በክልሉ በሚገኙ 1 ሺህ 722 ትምህርት ቤቶች በተደረገው ቅድመ ዝግጅት መሰረት መስከረም 14 ቀን 2016 ዓ.ም ትምህርት በይፋ መጀመሩንም አስታውቀዋል። ተማሪዎች ከበዓላት ጋር ተያይዞ በወቅቱ መጥተው ያለመመዝገባቸው እና የክልል አቀፍ ፈተና ከወሰዱት የማለፊያ ውጤት ያመጡት ተማሪዎች ቁጥር አናሳ ሆኖ መገኘቱ በተወሰነ ደረጃ የተመዝጋቢ ቁጥሩን እንዲቀንስ ያደረገ መሆኑን አንስተዋል ። በተቀመጠው ሀገራዊ የትምህርት ማስጀመሪያ ሰሌዳ መሰረት በክልሉ በሁሉም ትምህርት ቤቶች የመማር ማስተማር ስራ ተጀምሮ እየተከናወነ መሆኑን ዶክተር ደስታ አመልክተዋል። በክልሉ በ2016 የትምህርት ዘመን የተሻለ ውጤት የሚመዘገብበት ለማድረግ መታቀዱን ገልጸው ለዚህ እንዲረዳ በቂ ቅድመ ዝግጅት ተደርጎ ወደ ተግባር መገባቱን ገልጸዋል። በክረምት ወቅት ለትምህርት ጥራት መጠበቅ የሚረዱ የመማሪያ ክፍሎችና የመምህራን መኖሪያን ጨምሮ የተለያዩ ግንባታዎች፣ ትምህርት ቤቶችን ማስዋብ፣ የስልጠናና የውይይት ሥራዎች ተሰርተዋል ብለዋል። ትምህርት ቤቶች ከቀድሞው በተሻለ መልኩ ለመማር ማስተማር ምቹ የማድረግ ሥራና መምህራንና ተማሪዎች ተሟልተው መገኘታቸውን በማረጋገጥ የማስጀመሪያ መርሃ ግብር መከናወኑን ገልጸዋል። በ2016 የትምህርት ዘመን 784 ተማሪዎችን መዝግቦ ለማስተማር መታቀዱን የገለፁት የባርታ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር አስራት ሀይሌ ናቸው። በታቀደው መሰረት የምዝገባ ሂደት ተጠናቅቆ ከመስከረም 14 ቀን 2016 ዓም ጀምሮ ወደ መማር ማስተማር ሥራ መግባታቸውን ገልፀዋል። በተለያዩ በዓላት ምክንያት መንጠባጠቦች እንዳይኖሩ ወላጆች ተማሪዎችን ሀላፊነት ወስደው እንዲልኳቸውም ጥሪያቸውን አቅርበዋል። የትምህርት አጀማመርን አስመልክተው ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት የግራዝማች ጳውሎስ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ርዕሰ መምህር ሊባኖስ ተመስገን፣ በክረምቱ ትምህርት ቤቱን የማስዋብና ለመማር ማስተማር ሥራው ምቹ የማድረግ ስራ ሲከናወን መቆየቱን ጠቁመዋል። ተማሪዎችን የመመዝገብ ስራ በማጠናቀቅ ከቅድመ ዝግጅት ስራዎች ውስጥ ዋና ተግባር መሆኑን ጠቁመው፣ ለመመዝገብ በታቀደው መሰረት በማከናወን ወደ ተግባር መገባቱን ጠቁመዋል ። ዘንድሮ ትምህርት በአዲሱ ካሪኩለም የሚሰጥ በመሆኑ የሚባክን የትምህርት ጊዜ እንደማይኖር የገለፁት መምህር ሊባኖስ፣ የተማሪ ወላጆችም ይህን በተገቢው ተረድተው ለልጆቻቸው ተገቢውን ክትትልና ድጋፍ እንዲያደርጉም አሳስበዋል። የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል በተያዘው የትምህርት ዘመን ከ6 መቶ 47 ሺህ በላይ ተማሪዎችን በመመዝገብ ወደ መማር ማስተማር ሥራ መግባቱን በትምህርት ቢሮው በኩል ማስታወቁ አይዘነጋም።
የቢሾፍቱን የኮንፈረንስ ቱሪዝም መዳረሻነት የሚያሳድጉ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ ነው - የከተማዋ አስተዳደር
Sep 29, 2023 62
አዲስ አበባ ፤ መስከረም 18 /2016 (ኢዜአ)፡-የቢሾፍቱን የኮንፈረንስ ቱሪዝም መዳረሻነት የበለጠ ለማሳደግ የሚያስችሉ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን የከተማዋ አስተዳደር አስታወቀ። የከተማዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ ገዛኸኝ ደጀኔ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የቢሾፍቱ ከተማ በአገር ውስጥና በውጭ ቱሪስቶች በብዛት የምትጎበኝ ከተማ ነች። ከተማዋን የሚጎበኙ ቱሪስቶች የቆይታ ጊዜያቸው እንዲጨምር ትኩረት ተደርጓል ብለዋል። ከዚህ ጎን ለጎን የከተማዋን ተፈጥሯዊ መስህቦች በመጠቀም በኮንፈረንስ ቱሪዝም ተመራጭ እንድትሆን የተለያዩ የልማት ሥራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በተለይም የቱሪስት መዳረሻዎችን ማልማትና ደረጃቸውን ማሻሻል እንዲሁም የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓቱን የማዘመን ሥራ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል። ይህም ሥራ በመንግሥትና በግል ዘርፉ አጋርነት የሚከናወን መሆኑን በመጠቆም። እየተከናወኑ ካሉ ሥራዎች መካከል የአስፓልት መንገድ ሽፋን እንዲሁም የኤሌክትሪክና የውኃ አገልግሎትን ተደራሽነት ማስፋት ተጠቃሽ ናቸው ነው ያሉት። በየዓመቱ የሚከበረው የሆራ አርሰዲ የኢሬቻ በዓል ከገጽታ ግንባታ ባለፈ ለከተማዋ ትልቅ የገቢ ምንጭ መሆኑን ጠቁመው ይህንን ይበልጥ ለማጠናከር እየተሰራ ነው ብለዋል። የቢሾፍቱ ከተማ 62 ሺህ ሄክታር መሬት የምትሸፍን ሲሆን በሦስት ክፍለ ከተሞችና 10 ወረዳዎች መደራጀቷን የከተማ አስተዳደሩ መረጃ ያመለክታል።
በሲዳማ ክልል በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት 1 ሚሊዮን 640 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ሆነዋል- የክልሉ ሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ቢሮ
Sep 29, 2023 266
ሀዋሳ ፤ መስከረም18/2016 (ኢዜአ)፡- በሲዳማ ክልል በክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በተከናወኑ የልማት ሥራዎች 1 ሚሊዮን 640 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን የክልሉ ሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ቢሮ ገለፀ። በተደረገ እንቅስቀሴም ከመንግስት ይወጣ የነበረን 722 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ማዳን መቻሉም ተገልጿል። የቢሮው ምክትልና የወጣቶች ዘርፍ ኃላፊ አቶ ደስታ ለገሰ እንዳሉት በክረምት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት 13 ዋና ዋና ተግባራት ተለይተው ወደ ሥራ ተገብቷል። በእዚህም ከ731 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ የልማቱ ሥራዎችን በማከናወን 1 ነጥብ 6 ሚሊዮን የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ታቅዶ ወደሥራ መገባቱን አስታውሰዋል። እስካሁንም በተደረገ እንቅስቀሴ 722 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመቱ የልማት ተግባራት መከናወናቸውን ጠቅሰው፣ በዚህም ከመንግስት ይወጣ የነበረን ወጪን ማዳን ተችሏል ብለዋል። በማህበረሰብ አገልግሎት ከተከናወኑ ስራዎች መካከል የአረንጓዴ አሻራ ልማት፣ ደም ልገሳ፣ የሠላምና ፀጥታ፣ የትራፊክ አደጋ መከላከል፣ ሙያዊ የማጠናከሪያ ትምህርት፣ የአረጋዊያን ቤቶች እድሳትና ሌሎችንም ለአብነት ጠቅሰዋል። በበጎ ፍቃድ አገልግሎቱ ላይ ከ600 ሺህ በላይ ወጣቶች መሳተፋቸውን የጠቀሱት ኃላፊው፣ "በተከናወኑ የልማት ሥራዎችም 1 ሚሊዮን 640 ሺህ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ሆነዋል" ብለዋል;። ለደም ልገሳ የተለየ ትኩረት በመሰጠቱ ከወጣቶችና ከህብረሰቡ አበረታች ምላሽ እየተሰጠ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ደስታ፣ በክረምቱ ለመሰብሰብ ከታቀደው 2 ሺህ ዩኒት ደም እስካሁን ድረስ ከ2 ሺህ 500 ዩኒት በላይ ደም በመሰብሰብ ከዕቅድ በላይ ለማሳካት እንደተቻለ አስረድተዋል። አቶ ደስታ እንዳሉት በማህበረሰብ አቀፍ የበጎ ፈቃድ ተግባራት ወጣቶች የአቅመ ደካሞችን ቤት በማደስ፣ ለበዓል ማዕድ በማጋራት፣ የትምህርት ቁሶችን በመለገስ፣ የወጣት ማዕከላትን በማጠናከርና ሌሎች ድጋፎችን በማድረግ ተሳትፈዋል። "እስካሁንም ከ850 በላይ የአቅመ ደካሞች ቤት በወጣቶች፣ በመንግስት ተቋማትና በሌሎች አካላት ታድሰዋል" ብለዋል። በበጎ ፈቃድ አገልግሎት ቤታቸው ከታደሰላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች መካከል በይርጋዓለም ከተማ የሚኖሩት ወይዘሮ አማረች በዳኔ አንዷ ናቸው። በእድሜ ብዛት ለጉዳት የተዳረገችው ደሳሳ ቤታቸው ለጸሐይና ለዝናብ በማጋለጥ ለችግር ዳርጓቸው ሲኖሩ እንደነበር አስታውሰዋል። የቤቱ በርም በእርጅና ተጎድቶ ብዙ ጊዜ ክፍት በመሆኑ ለስርቆት ሲጋለጡ መቆየታቸውን ነው የተናገሩት። በአሁኑ ወቅት ቤታቸው በአዲስ መልክ በመሰራቱ መደሰታቸውን የገለፁት ወይዘሮ አማረች፣ "ከሰሞኑ ደህና እንቅልፍ እየተኛሁ ነው" ሲሉ ቤቱን ለሰሩላቸው ምስጋና አቅርበዋል። የሀዋሳ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ አስናቀች ኃይሉ በበኩላቸው በህመም ምክንያት ብዙም መንቀሳቀስ ከተሳናቸው ባለቤታቸውና ከአራት ልጆቻቸው ጋር በደሳሳ ጎጇቸው ውስጥ በአስቸጋሪ ሁኔታ ይኖሩ እንደነበር አስታውሰዋል። በደሳሳ ቤታቸው ንፋስ፣ ዝናብ እና ጎርፍ በቀላሉ ይገባ እንደነበር አስታውሰው፣ አሁን ላይ በብሎኬት የተገነባ ያማረ ቤት ተሰርቶ በመረከባቸው እፎይ ማለት መጀመራቸውን ገልፀዋል። በሲዳማ ክልል በክረምቱ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት እየተሳተፉ ካሉ ወጣቶች መካከል የሀዋሳ ከተማ ነዋሪ ወጣት እድላዊት አበራ በበኩሏ፣ "በጎ ሥራ ፈጣሪንና ሌሎች ሰዎችን የምናስደስትበት እኛ ደግሞ የህሊና እርካታን የምናገኝበት ትልቅ ፀጋ ነው" ብላለች። ከእነሱ በኋላ ለሚመጡ ትውልዶችም መልካም የሆነ ሥነ ምግባርን የሚያወርሱበት ተግባር በመሆኑ ደስ ብሏቸው እንደሚሳተፉ ነው የገለጸቸው። ከአንድ ዓመት በፊት የ12ኛ ክፍል ብሔራዊ ፈተና መውሰዷን የተናገረቸው ወጣቷ፣ በሀዋሳ መሀል ክፍለከተማ በሚገኝ የወጣቶች ማዕከል ቤተ መጻህፍት ውስጥ ስታገለገል መቆየቷን ገልፃለች። ቤተ መጻሕፍቱን ለማጠናከር የተለያዩ መጻህፍት መለገሷን ገልጻ፣ በቀጣይም የበጎ ፈቃድ ሥራዋን አጠናክራ እንደምትቀጥል አረጋግጣለች።
በጋምቤላ ክልል በጎርፍ ምክንያት ለተፈናቀሉ ወገኖች ድጋፍ ተደረገ
Sep 29, 2023 74
ጋምቤላ ፤ መስከረም 18 /2016(ኢዜአ) ፡- የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር በጋምቤላ ክልል ሰሞኑን ተከስቶ በነበረው የጎርፍ አደጋ ለተፈናቀሉ ወገኖች ከ3 ሚሊዮን ብር በላይ ግምት ያላቸው ቁሶች ድጋፍ ማድረጉን አስታወቀ። በማህበሩ የጋምቤላ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቼንኮት ዴቪድ ፤ ማህበሩ ድጋፉን ያደረገው ጋምቤላ ከተማን ጨምሮ በአምስት ወረዳዎች አቅመ ደካሞችን ጨምሮ ከፍተኛ ጉዳት ላጋጠማቸው 475 እማወራዎችና አባወራዎች መሆኑን በድጋፍ ርክክብ ወቅት ገልጸዋል። ከድጋፉ ውስጥ ብርድ ልብስ፣ የመኝታና የዝናብ መከላከያ ፕላስቲክ፣ የውሃ ጄሪካንና የንጽህና መጠበቂያ ግብዓቶች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል። በጋምቤላ ከተማ አስተዳደር ከትናንት ጀምሮ ድጋፉን ማሰራጨት መጀመሩንና ቀሪዎቹን እንደሚቀጥል አስረድተዋል፡፡ ቀደም ሲልም ከ4 ሚሊዮን ብር በላይ የሚገመት ተመሳሳይ ድጋፍ ለ725 እማዎራዎችና አባዎራዎች መደረጉን አስታውሰው፤ ማህበሩ ሰብዓዊ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥልም ገልጸዋል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ተወካይ አቶ ኡሞድ ኡሞድ ፤ ማህበሩ በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች ለተጎዱ ፈጥኖ በመድረስ እያደረገ ላለው ሰብዓዊ ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። በክልሉ በቅርቡ ተከስቶ በነበረው የወንዞች ውሃ ሙላት ሳቢያ ከቤት ንብረታቸው ለተፈናቀሉ ወገኖች ማህበሩ ያደረገው ድጋፍ አንዱ ማሳያ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ጎርፍ ባስከተለው ችግር የተፈናቀሉ ወገኖችን የመደገፉ ተግባር በሌሎችም ተቋማት ተሳትፎ ሊጠናከር እንደሚገባም አመልክተዋል፡፡ በተከሰተው የጎርፍ አደጋ ቤታቸው ፈርሶ ለችግር መጋለጣቸውን የገለጹት የጋምቤላ ከተማ ነዋሪ አቶ ፒተር ኡፓቲ ናቸው። የቀይ መስቀል ማህበር ያደረገላቸው ድጋፍ በተወሰነ ደረጃ ችግራቸውን እንደሚያቃልላቸው ጠቁመው፤ ለተደረገላቸው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል። ወይዘሮ ተዋበች ብርሃኑ በበኩላቸው፤ የባሮ ወንዝ ሞልቶ በመፍሰስ በቤትና ንብረታቸው ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱን ተናግረዋል። በቀይ መስቀል ማህበሩ የተጀመረው ድጋፍ በሌሎች ድርጅቶችም ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል። በጋምቤላ ክልል ባሮን ጨምሮ ሌሎችም ወንዞች ሞልተው በመፍሰስ ባስከተሉት ጎርፍ በጋምቤላ ከተማ አስተዳደርና በዘጠኝ ወረዳዎች ነዋሪዎች መፈናቀላቸው ቀደም ብሎ ተገልጿል።
በሰመራ ሎጊያ ከተማ ወንጀልን ለመከላከል በማህበረሰብ ተሳትፎ በተከናወኑ ሥራዎች ውጤት ተገኝቷል--የከተማው ፖሊስ
Sep 29, 2023 70
አፋር፤ መስከረም 18/2016 (ኢዜአ) ፡-በሰመራ ሎጊያ ከተማ ወንጀልን ለመከላከል ማህበረሰቡን በማሳተፍ በተከናወኑ ቅንጅታዊ ሥራዎች ውጤት እየተገኘ መምጣቱን የከተማው ፖሊስ አስታወቀ። የከተማዋ ነዋሪዎች በበኩላቸው ማህበረሰቡ ከፖሊስ ጋር በመሆን እያከናወናቸው ባሉ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች ወንጀል ከመከላከል ባለፈ የተሻለ ደህንነት እየተሰማቸው መሆኑን ተናግረዋል። በከተማዋ የቀበሌ 04 የማህበረሰብ ፖሊሲንግ አስተባባሪ አቶ መሐመድ አስኑም እና የከተማዋ ፖሊስ አባል አቶ ሳሊህ አህመድ እንዳሉት ቀደም ሲል በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የስርቆት ወንጀሎች ሲፈጸሙ ነበር። ከማህበረሰቡ ጋር በመቀናጀት ሌት ተቀን እየተከናወነ ባለው ወንጀልን በጋራ የመከላከልና የጸጥታ ሥራ ተጨባጭ ውጤት መገኘቱን ገልጸዋል። በእዚህም በከተማዋ ባለፉት ጊዜያት ወንጀል ሲፈፅሙ የነበሩ ሰዎች በቁጥጥር ስር በመዋላቸው የሚፈጸም የስርቆት ወንጀል በእጅጉ መቀነሱን ተናግረዋል። ህብረተሰቡን ከስርቆት፣ ከንጥቂያና ከዘረፋ ወንጀሎች ለመታደግ እየተከናወኑ ያሉ የማህበረሰብ አቀፍ የአካባቢ ጥበቃ ሥራዎች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል። በሰመራ ከተማ መስተዳድር ሰላምና ፀጥታ ፅህፈት ቤት የፈዴራሊዝም አስተምህሮ ሥርዓት ቡድን መሪ አቶ መሃመድ ዓሊ በበኩላቸው የከተማዋን ሰላምና ጸጥታ ይበልጥ ለማጠናከር ማህበረሰቡን ያሳተፈ ሥራ እየተሰራ ነው ብለዋል። ወንጀልን ቀድሞ በመከላከል ተግባር ማህበረሰቡ የበኩሉን እንዲወጣ ግንዛቤ ከማስጨበጥ ባለፈ የሥራው አካል ማድረግ መቻሉን ገልጸው፣ በእዚህም ህብረተሰቡን ከጸጥታ አካላት ጋር በማቀናጀት ሥራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውን ገልጸዋል። በከተማዋ የተለያዩ የስርቆት ወንጀሎች ተበራክተው እንደነበር ያስታወሱት ቡድን መሪው፣ ማህበረሰቡን በማሳተፍ እየተከናወኑ ባሉ ወንጀልን ቀደሞ የመከላከል ሥራዎች የስርቆት ወንጀል በእጅጉ እየቀነሰ መምጣቱን ገልጸዋል። በከተማ አስተዳደሩ የተዋቀረው የማህበረሰብ አቀፍ ፖሊሲንግ አገልግሎት አባላት የራሳቸውን ሀላፊነት እየተወጡ መምጣታቸው ለተገኘው ውጤት የጎላ ሚና እንዳለውም አስረድተዋል። በተለያዩ የከተማዋ አካባቢዎች 950 ሰዎች የማህበረሰብ አቀፍ ፖሊሲንግ ስልጠና ወስደው ወደስራ እንዲገቡ መደረጉን የገለጹት ደግሞ የከተማ መስተዳድሩ ሠላምና ፀጥታ ፅህፈት ቤት ኀላፊ አቶ አብዱ ኢሴ ናቸው። ከማህበረሰቡ ጋር በቅንጅት በተከናወኑ ሥራዎች በከተማዋ ሲስተዋሉ የነበሩ አብዛኞቹ የወንጀል ድርጊቶች እየተፈቱ መምጣታቸውን ገልጸዋል። ህብረተሰቡ ለፖሊስ ተባባሪ ሆኖ በመስራቱ ወንጀል የሰሩ ሰዎች ህብረተሰቡ ውስጥ እንዳይደበቁ ማድረግ መቻሉንም አቶ አብዱ አስረድተዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የሰመራ ሎጊያ ከተማ ነዋሪዎች መካከል አቶ ከድር ሰይድ በከተማዋ ባለፉት ጊዜያት ተደጋጋሚ ስርቆቶች ሲፈጸሙ እንደነበር አስታውሰው፣ "በአሁኑ ወቅት ህዝብን በማሳተፍ እየተከናወኑ ባሉ የወንጀል መከላከል ሥራዎች የሰላም እንቅልፍ እየተኛን ነው" ብለዋል። ፖሊስ እና ማህበረሰቡ በቅንጅት እያከናወኑት ባለው ሥራ በከተማዋ ቀድሞ የነበረው የሌብነት ወንጀል እየቀረ መምጣቱን የገለጹት ደግሞ ወጣት ሱሌ አሊ እና አብደላ ሁመድ ናቸው። "ተከታታይነት ያለው የማህበረሰብ አቀፍ ፖሊሲንግ ስራ በመሠራቱ የስርቆት ወንጀል ጭራሽ ቆሟል ማለት ባይቻልም ቀንሷል፤ የተሻለ ሰላምና እፎይታ አግኝተናል" ብለዋል። በዋናነት በባጃጆች የታገዘ የስርቆት ወንጀል ይካሄድ እንደነበረ አስታውሰው የተቀናጀ ሥራ በመሰራቱ በአሁኑ ወቅት ወንጀል በእጅጉ መቀነሱን ተናግረዋል።
ከሦስት ሚሊዬን በላይ ዜጎች ብሔራዊ መታወቂያ ለማግኘት ተመዝግበዋል - የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ጽህፈት ቤት
Sep 29, 2023 114
አዲስ አበባ፣ መስከረም 18/2016 (ኢዜአ)፦ ከሦስት ሚሊዬን በላይ ዜጎች ብሔራዊ መታወቂያ ለማግኘት የሚያስችላቸውን ምዝገባ ማድረጋቸውን የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ጽህፈት ቤት ገለጸ። የዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት ባለፉት ሦስት ዓመታት በኢትዮጵያ የሙከራ ትግበራ ላይ የሚገኝ ሲሆን በ2015 ዓ.ም የዲጂታል መታወቂያ አዋጅ ጸድቆ ወደ ሥራ መግባቱ ይታወሳል። የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ጽህፈት ቤት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ራሔል አብርሃም ለኢዜአ እንደገለጹት በተያዘው የበጀት ዓመት 25 ሚሊዬን ዜጎች መታወቂያውን እንዲያገኙ እየተሰራ ነው። አሁን ላይ ከሦስት ሚሊዬን በላይ ዜጎች የብሔራዊ መታወቂያ ለማግኘት ምዝገባ ማድረጋቸውን ገልጸው የምዝገባው ሥራ ከተለያዩ አጋር አካላት ጋር በትብብር እየተከናወነ እንደሚገኝ አመልክተዋል። የዲጂታል መታወቂያው የቀበሌ መታወቂያን ለመተካት ሳይሆን የዲጂታል መታወቂያ አገልግሎት ሰጪዎች የግለሰቦችን ማንነት እንዲለዩ ታሳቢ በማድረግ የተዘጋጀ እንደሆነም ጠቁመዋል። በመሆኑም ብሔራዊ መታወቂያ በኢትዮጵያ የሚኖር ማንኛውም ዜጋ የራሱን ማንነት የሚገልጽበት መለያ መሆኑን ተናግረው የመታወቂያው ዓላማ ዜጎች የማንነት ማረጋገጫ በማሳየት አገልግሎት እንዲያገኙ ማስቻል ነው ብለዋል። በቀጣይ ሁኔታዎችን በማየት የዲጂታል መታወቂያና የቀበሌ መታወቂያ በተመጋጋቢነት ሊሰሩ የሚችሉበት ሁኔታ እንደሚፈጠርም ነው ያብራሩት። የብሔራዊ መታወቂያ ዜጎች ጊዜና ቦታ ሳይወስናቸው በኤሌክትሮኒክስ አማራጭ የተለያዩ አገልግሎቶችን በቀላሉ እንዲያገኙ በማስቻል ረገድ ቁልፍ ሚና እንደሚኖረው ገልጸዋል። በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት 90 ሚሊዬን ዜጎችን የብሔራዊ መታወቂያ ባለቤት ለማድረግ መታቃዱን ከብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ጽህፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመለክታል። እቅዱ የተፈናቀሉ ዜጎች፣ ሰብአዊ እርዳታ የሚያሻቸውና ሌሎች ማንነታቸውን የሚያረጋግጥ መረጃ ማቅረብ የማይችሉ ዜጎችን ታሳቢ ማድረጉ ተገልጿል።
የይርጋጨፌ ቡና ገበሬዎች ህብረት ስራ ዩኒየን ከ45 ሺህ ለሚልቁ ተማሪዎች ድጋፍ አደረገ
Sep 29, 2023 84
ዲላ ፤ መስከረም 18/ 2016 (ኢዜአ)፡- የይርጋጨፌ ቡና ገበሬዎች ህብረት ስራ ዩኒየን ከ11 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ በማድረግ ድጋፍ ለሚሹ ከ45 ሺህ ለሚልቁ ተማሪዎች የትምህርት ቁሳቁስ ማበርከቱን አስታወቀ። ዩኒየኑ በዞኑ አንድም ተማሪ በትምህርት ቁሳቁስ እጦት ሳቢያ ከትምህርት ቤት እንዳይርቅ የሚደረገውን ጥረት በማገዝ ማህበራዊ ሃላፊነቱን እየተወጣ መሆኑንም ገልጿል። በዩኒየኑ የዲላ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ክፍሌ አየለ እንዳሉት፤ ድጋፉ በ28 አባል ህብረት ስራ ማህበራት በኩል ለተማሪዎች እየተሰራጨ ነው። በዚህም በጌዴኦ ዞን ድጋፍ የሚሹ ከ45 ሺህ በላይ የአርሶ አደር ልጆች ተጠቃሚ እንደሚሆኑና ለትምህርት ቁሳቁሶቹ ከ11 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ መደረጉን አስታውቀዋል። ድጋፉም ደብተር፣ እስክርቢቶና ሌሎች የመማሪያ ቁሳቁሶችን ያካተተ መሆኑን ጠቅሰዋል። ዩኒየኑ በዞኑ አንድም ተማሪ በደብተር እጦት ሳቢያ ቤት እንዳይውል የሚደረገውን ጥረት እያገዘ መሆኑን የገለጹት የጌዴኦ ዞን ትምህርት መምሪያ ሃላፊ ተወካይ አቶ ብርሃኑ ዘውዴ ናቸው። ዩኒየኑ የቡና አምራች አርሶ አደሩን የገበያ ችግር በማቃለል የተሻለ ዋጋ እንዲያገኝ ከማድረግ ባለፈ ድጋፍ ለሚሹ የአርሶ አደር ልጆች ድጋፍ ማድረጉ የሚበረታታ መሆኑን ተናግረዋል። ድጋፍ ከተደረገላቸው የተማሪ ወላጆች መካከል አርሶ አደር ኤፍሬም ታደሰ በሰጡት አስተያየት፤ ዩኒየኑ ያደረገው እገዛ ልጆቻችንን በምን እናስተምራለን ብለን እንዳንጨነቅ ያደረገ ነው ብለዋል።
በዓላቱ የሰላምና አንድነት ተምሳሌት መሆናቸውን በተግባር እያሳየን ቀጥለዋል- የአክሱምና መቀሌ ነዋሪዎች
Sep 28, 2023 95
አክሱም/መቀሌ፤ መስከረም 17/2016(ኢዜአ)፡-የመውሊድ፣ የደመራና የመስቀል በዓላት የሰላም፣ የአንድነትና የመደጋገፍ ተምሳሌት በመሆን አብሮነትን በተግባር ማሳየት የተቻለባቸው ናቸው ሲሉ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአክሱምና መቀሌ ከተሞች ነዋሪዎች ገለጹ። ኢትዮጵያዊ አስተሳሰብ ይዘን ለሃይማኖት እኩልነትና ልማት በፍቅርና አንድነትና ልንሰራ ይገባል ሲሉም የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሃላፊ ሼክ አደም ዓብደልቃድር ገልጸዋል። ከአክሱም ከተማ ነዋሪዎች ሐጂ መሐመድ ሰዒድ ወሃብ እንደገለጹት፤ የመውሊድ በዓልን ያከበሩት የሌላቸውን ወገኖች በማሰብና ማዕድ በማጋራት ነው። የዘንድሮ መውሊድና የደመራ በዓላት በተመሳሳይ ቀን መዋላቸው መቻቻል መከባበርና አንድነትን ለማጠናከር ምቹ ሁኔታ መፍጠራቸውንም ተናግረዋል። የሁለቱም ሃይማኖቶች ተከታዮች እንደ ቀድሞ ሁሉ በዓላቱ የሰላም፣ የአንድነትና የመደጋገፍ ተምሳሌት በመሆን አብሮነትን በተግባር ማሳየት እንደተቻለባቸውም ገልጸዋል። ሌላው የአክሱም ከተማ ነዋሪ ቆመስ አባ ዮሐንስ ገብረማሪያም በበኩላቸው፤ በከተማውና አካባቢው የእስልምና እና የክርስትና እምነት ተከታዮች የመውሊድና የመስቀል በዓላትን በጋራ በማክበር የቆየ አብሮነታቸውን አጠናክረው ቀጥለዋል ብለዋል። የመውሊድ፣ ደመራና የመስቀል በዓላት ዘንድሮ በተመሳሳይ ቀን መዋላቸው የሁለቱም እምነቶች ተከታዮች ተቻችለውና ተከባብረው በፍቅር አብሮ የመኖር ዘመን ተሻጋሪ ባህላቸው ይበልጥ ጠንክሮ እንደሚቀጥል አብነት መሆኑን ገልጸዋል። በመቀሌ የሃወልቲ ክፍለ ከተማ ነዋሪዎች ሃጅ ስዒድ ህሴን የእስልምና እምነት ተከታይ ሲሆኑ፣ አቶ ዳንኤል ዛይድ ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን እምነት ተከታይ ናቸው። ነዋሪዎቹ እንዳሉት ከቤተሰቦቻቸው ጋር በመሆን የሁለቱንም ሃይማኖታዊ በዓላትን ለ20 ዓመታት አብረው በአንድነትና በአብሮነት አሳልፈዋል። በጋራ ማክበር ብቻ ሳይሆን ካላቸው ቀንሰው ለተቸገሩ ወገኖች በማካፈል ሲደግፉ መቆየታቸውን እና ዘንድሮም ይህንኑ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። ሃይማኖታዊ በዓላትን በጋራ ከማክበር ባለፈ ቤተ-እምነቶቻቸውን በጋራ በመጠገንና በአዲስ በመስራትም ትብብራቸው ጥብቅ መሆኑን አስረድተዋል። በአንድ ቀን የተከበሩት የመውሊድና የደመራ በዓላት በጋራ ሲከብሩ በተለያየ መክንያት ለችግር ተዳርገው ድጋፍ የሚሹ ወገኖችን በመጠየቅና በማገዝ እንደሆነም ተናግረዋል። የትግራይ ክልል እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ሃላፊ ሼክ አደም ዓብደልቃድር በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያዊ አስተሳሰብ ይዘን ለሃይማኖት እኩልነትና ልማት በፍቅርና አንድነትና ልንሰራ ይገባል ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የትግራይን የመስህብ ስፍራዎች በአግባቡ በማስተዋወቅ ከዘርፉ ተጠቃሚ ለመሆን ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል- አቶ ጌታቸው ረዳ
Sep 28, 2023 94
መቀሌ፤ መስከረም 17/2016(ኢዜአ)፦በትግራይ ክልል የሚገኙ የቱሪዝም የመስህብ ስፍራዎችንና ቅርሶችን በአግባቡ ጠብቆ በማስተዋወቅ ከዘርፉ ተጠቃሚ ለመሆን እየተደረገ ባለው ጥረት ሁሉም የድርሻውን ሊወጣ ይገባል ሲሉ የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ-መስተዳድር አቶ ጌታቸው ረዳ ገለፁ። የደመራ በዓል በዓዲግራት ከተማ ርዕሰ መስተዳድሩን ጨምሮ የሃይማኖት አባቶችና ምዕመናን በተገኙበት ዛሬ በደማቅ ሥነ-ሥርዓት ተከብሯል። አቶ ጌታቸው በዚሁ ጊዜ የተገኘውን ሰላም ተጠቅመን በዓሉን ማክበር እንደቻልነው ሁሉ፤ በክልሉ የሚገኙ የመስህብ ስፍራዎችን እየጠበቅን የቱሪስት መዳረሻ ልናደርጋቸው ይገባል ብለዋል። የትግራይ መልሶ ግንባታን ለማፋጠን የተጀመረው የተቀናጀ ጥረት ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አቶ ጌታቸው አረጋግጠዋል። በየደረጃው የሚገኙ የህዝብ ተወካዮች፣ የሃይማኖት አባቶችና ምሁራን የድርሻቸውን እንዲወጡም መልዕክት አስተላልፈዋል። የክብረ-በዓሉ ታዳሚዎች በበኩላቸው ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን ከመንግሥት ጎን ሆነው የሚጠበቅባቸውን ሁሉ እንደሚወጡ ገልጸዋል።
በሽናሻ ብሄረሰብ ባህል ቂም ይዞ ወደ አዲሱ ዓመት መሸጋገር ፈጽሞ አይቻልም - የሽናሻ የሀገረ ሽማግሌዎች
Sep 28, 2023 77
አሶሳ (ኢዜአ) መስከረም 17/2016፡- በሽናሻ ብሄረሰብ ባህል ቂም ይዞ ወደ አዲሱ ዓመት መሸጋገር ፈጽሞ አይቻልም ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው የብሄረሰቡ የሀገር ሽማግሌዎች ገለጹ፡፡ የሽናሻ ብሄረሰብ ዘመን መለወጫ በዓል “ጋሪ ዎሮ” በአሶሳ ከተማ በተለያዩ ዝግጅቶች ዛሬ በድምቀት ተከብሯል፡፡ ከብሄረሰቡ የሃገር ሽማግሌዎች አቶ ለማ አልጋ እንዳሉት በሽናሻ ብሄረሰብ ቂም ይዞ ወደ አዲሱ ዓመት መሸጋገር ፈጽሞ አይቻልም፡፡ በዚህም የአዲስ ዓመት እቅድ ከመዘጋጀቱ በፊት የተጣላ ካለ ተፈልጎ እርቅ እንዲወርድ ይደረጋል ያሉት አቶ ለማ ይህን ተከትሎ የሃገር ሽማግሌዎች ይመርቃሉ ብለዋል፡፡ ሌላው የብሄረሰቡ ሀገር ሽማግሌ አቶ አሰፋ ታዬ በበኩላቸው ከምንም በፊት ለሠላም እና ለፍቅር ቅድሚያ መስጠት የአባቶቻችን ባህላዊ እሴት ነው ብለዋል፡፡ ያለ ሠላም የሚከናወን ምንም ጉዳይ እንደሌለ ገልጸው፤ የሃሳብ ልዩነትን እንዲከበር ከማድረግ ጀምሮ አለመግባባቶች በግልጽ ንግግር እንዲፈቱ በማድረግ ሃላፊነታቸው እንደሚወጡም አረጋግጠዋል፡፡ የብሄረሰቡ ባህላዊ እሴቶች በአግባቡ ተጠብቀው ለትውልድ ማስተላለፍ ከተቻለ ለሀገር ያለውን ጠቀሜታ የሚናገሩት ደግሞ አቶ ተስፋሁን ኪሉ ናቸው፡፡ የብሄረሰቡን ባህል ተጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍና በተለይ ወጣቱ ትውልድ በውል እንዲገነዘበው ከማድረግ ባሻገር በማህበረሰቡ ዘንድ ያላቸውን ተሰሚነትና ተቀባይነት ተጠቅመው አንድነትንና አብሮነትን ማጠናከር ዋነኛ ትኩረታቸው እንደሚሆን የብሄረሰቡ የሀገር ሽማግሌዎቹ ገልጸዋል፡፡
በአዲስ አበባ የሰው ተኮር ፕሮጀክቶች ግንባታ የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ባሳተፈ መልኩ ተጠናክሮ ይቀጥላል- ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Sep 28, 2023 82
አዲስ አበባ፣ መስከረም 17/2016 (ኢዜአ)፦ የሰው ተኮር ፕሮጀክቶች ግንባታ የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ባሳተፈ መልኩ ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ፤ በጉለሌ ክፍለ ከተማ የተገነባውን 20ኛውን የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከል መርቀው ለአገልግሎት ክፍት አድርገዋል። በዚሁ መርሃ-ግብር ላይ መልዕክት ያስተላለፉት ከንቲባ አዳነች አቤቤ፤ የሰው ተኮር ፕሮጀክቶች ግንባታ የተለያዩ የሕብረተሰብ ክፍሎችን ባሳተፈ መልኩ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። የሰው ተኮር ፕሮጀክቶች ግንባታ በባለሃብቶችና ሌሎችም የኅብረተሰብ ክፍሎች የገንዘብ፣ የእውቀትና የክህሎት ድጋፍ እየተከናወነ መቀጠሉን ገልፀዋል። የፕሮጀክቶቹ እውን መሆን የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ለሚደረገው ጥረት አጋዥ መሆናቸውን ከንቲባዋ ጠቅሰዋል። በመሆኑም ለፕሮጀክቶቹ መሳካት አስተዋጽዖ ላደረጉ ሁሉ ክብርና ምስጋና በማቅረብ በቀጣይም ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ከንቲባ አዳነች ጠይቀዋል። የከተማ አስተዳደሩ ምገባ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ሽታዬ መሀመድ፤ ከሰኔ 2014 ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን 20 የምገባ ማዕከላት በተሳካ መልኩ ተገንብተው ለኅብረተሰቡ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ገልፀዋል። በጉለሌ ክፍለ ከተማ በቀጨኔ መድኃኔዓለም አካባቢ የተሰራው 20ኛው የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከል በቶኩማ ስታር ቢዝነስ ግሩፕ በ47 ሚሊየን ብር ወጪ ነው የተገነባው። የጉለሌው የምገባ ማዕከል በቀን ከ500 የሚልቁ የአካባቢውን ነዋሪዎች የሚመግብ መሆኑ ታውቋል። በአዲስ አበባ እስካሁን የተገነቡት የምገባ ማዕከላት በቀን ከ35 ሺህ በላይ ወገኖችን የምገባ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ።
ለክልሉ ልማት ህዝቡን በማስተባባር በቁርጠኝነት መንቀሳቀስ ጀምረናል- የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ መስተዳድር
Sep 28, 2023 67
መቀሌ፤ መስከረም 17 ቀን 2016 (ኢዜአ)፡- የትግራይ ክልል ገዚያዊ አስተዳደር ለክልሉ ልማትና እድገት ህዝቡን በማስተባበር መንቀሳቀስ መጀመራቸውን የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ርዕሰ መስተዳደር አቶ ጌታቸው ረዳ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳደሩ ለመስቀል በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። አቶ ጌታቸው በመልዕክታቸው እንደገለጹት የክልሉን እምቅ ሀብት በአግባቡ ሰራ ላይ በማዋልና የህዝቡን አቅም በማስተባበር ክልሉን ለማልማትና ለማሳደግ በትኩረት መንቀሳቀስ ተጀምሯል። የመስቀል በዓል ከትናንት ዋዜማው ጀምሮ በክልሉ በተለያዩ ሃይማኖታዊ ክዋኔዎች በመከበር ላይ ይገኛል። በመቀሌ ከተማ በቅርብ ርቀት ላይ በሚገኘው በ”ጮምዓ“ ተራራ ላይ ትናንት በተከበረው የመስቀል ደመራ በዓል ላይ በክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የከተማው ከንቲባ አቶ ይትባረክ አምሃ ባስተላለፉት መልዕክት ላይ እንደገለጹት፤ "ጮምዓ" ተራራን በአግባቡ በማልማት ለቱሪዝም መስህብነት በማዋል ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ እንዲኖረው ትኩረት ይደረጋል። ተራራው ለከተማው ውበትና ሳቢነት ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ በመሆኑ አካባቢውን ለማልማት ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ተቀናጅተን መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። ከበዓሉ ታዳሚዎች መካከል የመቀሌ ከተማ ነዋሪዋ ወይዘሮ ፍፁም ነጋሽ በሰጡት አስተያየት፤ "ሰላም ተፈጥሮ የመሰቀል በዓሉን ለማክበር በመቻላችን ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶኛል" ሲሉ ገልጸዋል። ለመቀሌ ከተማ ግርማ ሞጎሰ ባለው” ጮምዓ” ተራራ ላይ የመሰቀል በዓልን በማክበሬ ተደስቼያለሁ ያለው ደግሞ ወጣት ሞገስ መኮንን ነው
የመስቀል በዓል ከደመራ ሥነ-ሥርዓት ጋር በጎንደር፣ በገንዳ ውሃና በሰቆጣ ዛሬ እየተከበረ ይገኛል
Sep 28, 2023 80
ጎንደር/መተማ/ሰቆጣ ፤ መስከረም 17/2016 (ኢዜአ)፦ የመስቀል በዓል ከደመራ ሥነ-ሥርዓት ጋር በጎንደር፣ በገንዳ ውሃና በሰቆጣ ከተሞች ሃይማኖታዊ ስርዓቱንና ባህላዊ እሴቱን በጠበቀ መንገድ ዛሬ እየተከበረ ይገኛል፡፡ በጎንደር ከተማ እየተከበረ ባለው በዓል ላይ የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብጹዕ አቡነ ዮሃንስ በዓሉን አስመልክተው ባስተላለፉት መልዕክት፤ እግዚአብሄር የሰጠንን ዓመቱንና በዓላትን ለሰላምና ለአንድነት ማጎልበት ልንጠቀምበት ይገባል ብለዋል፡፡ መስቀል የሰላም የአንድነትና የፍቅር ልዩ ምልክት በመሆኑ ሃይማኖታዊ እሴቱ ተጠብቆ ከትውልድ ትውልድ እንዲሻገር ህዝበ ክርስቲያኑ በአብሮነት መስራቱን አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል፡፡ የጎንደር ከተማ ከንቲባ ተወካይ አቶ ግርማይ ልጃለም በበኩላቸው የመስቀል ደመራ በአል ሰላማዊና በደመቀ መልኩ መከበሩ የህዝቡን ሰላም ፈላጊነትና ጨዋነት አጉልቶ ያሳየ መሆኑን ተናግረዋል። በተመሳሳይ የመስቀል በዓል ስናከብር ጥላቻን በማስወገድ ፍቅርና አንድነትን በሚያፀና መልኩ መሆን እንዳለበት የገለፁት ደግሞ የምዕራብ ጎንደር ዞን ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የሲኖዶሱ አባል ብጹዕ አቡነ ሰላማ ናቸው። በዓሉን ስናከብርም ያለው ለሌለው በማካፈልና ለወንድሙ ፍቅርን በመግለፅ መሆን እንዳለበት ጠቅሰው፤ ይህ በጎ ተግባር በዚህ ቀን ተወስኖ መቅረት እንደሌለበትና ዘላቂ መሆን እንዳለበት አሳስበዋል። የዞኑ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ አቶ አባተ ነጋ በበኩላቸው፤ የበዓሉ መገለጫ አንድነት፣ ፍቅርና ሰላም ነው ብለዋል። ምዕመኑ በአደባባይ ወጥቶ በዓሉን እንደከዚህ ቀደሙ ሁሉ ያሳለፈው ሰላም በመኖሩ ነውና ቀጣይም ሰላሙን ማስጠበቅ እንዳለበት ጠቁመዋል። "በዓሉ ድምቀቱን በጠበቀ መልኩ እንዲከበር በማድረግ የሌሎች እምነት ተከታዮችም ድርሻ የጎላ ነው" ያሉት ደግሞ የገንዳ ውሃ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ አብዱልከሪም ሙሃመድ ናቸው። በዓሉ በሰላምና በድምቀት እንዲከበር የከተማዋ ወጣት ላበረከቱት አስተዋፅኦ አመስግነው፤ በቀጣይም ይህን ተግባር አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል። በሌላ በኩል የዋግ ኽምራ ዞንና በሰቆጣ ከተማም በዓሉ በልዩ ልዩ ሃይማኖታዊ ክዋኔዎች እየተከበረ ነው። የዋግ ኽምረ ዞን ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ በርናባስ እንዳሉት መስቀል የምህረት የፍቅር ተምሳሌት በመሆኑ ምእመኑ ለሰላም ዘብ መቆም አለበት። የሰቆጣ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ መላሽ ወርቃለማው በበኩላቸው፤ በመስቀል በዓል የታየው አንድነትና መተባበር ተጠናክሮ በልማቱና በሌሎች ተግባራትም ሊቀጥል ይገባል ብለዋል። የመስቀል በአል በጎንደር፣ ገንዳ ውሃና ሰቆጣ ከተሞች የእምነቱ አባቶችና የየከተሞቹ አመራሮችና ምዕምናኑ በተገኙበት በድምቀት እየተከበረ ነው።
የመስቀል ደመራ በዓል ሰዎች በሕይወት ዘመናቸው ሊታደሙበት የሚገባ ልዩ ሁነት ነው- የተለያዩ አገራት ቱሪስቶች
Sep 28, 2023 72
አዲስ አበባ፣ መስከረም 17/2016 (ኢዜአ)፦ የመስቀል ደመራ በዓል ሰዎች በሕይወት ዘመናቸው ሊታደሙባቸው ከሚገቡ ልዩ ሁነቶች መካከል አንዱ ሊሆን ይገባል ሲሉ የተለያዩ የውጭ አገራት ቱሪስቶች ተናገሩ። የ2016 ዓ.ም የመስቀል ደመራ በዓል በተለያዩ ስነ ስርዓቶች በደማቅ ሁኔታ ተከብሯል። በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተካሄደው የመስቀል ደመራ በዓል አከባበር ላይ ወረብ እና ከተለያዩ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናት የተወጣጡ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችም ልዩ ልዩ ዝማሬዎችን አቅርበዋል። በበዓሉ ላይ ከታደሙት የውጭ ዜጎች መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው የውጭ አገራት ጎብኚዎች በሁነቱ መደመማቸውንና መደሰታቸውን ገልጸዋል። አሜሪካዊዩ ግራንት ቡሼ፤ ኢትዮጵያን የመጎብኘት ፍላጎት የረጅም ጊዜ እቅዳቸው እንደነበር ጠቅሰው በመስቀል በዓል ላይ ተገኝተው ድንቅ ነገሮችን በማየታቸው መደሰታቸውን ተናግረዋል። በእንዲህ አይነት ሁነቶች ላይ ሌሎችም ተገኝተው የኢትዮጵያን ድንቅ ሃብቶች እንዲጎበኙም ጋብዘዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክፍልን ገጽታዎች፣ አኗኗርና ትውፊት ቀደም ብለው መጎብኘታቸውን ጠቅሰው እምቅ የሆኑ የኢትዮጵያ ሃብቶችን በቀጣይነት ለዓለም ማስተዋወቅ ይገባል ብለዋል። ከእንግሊዝ የመጡት ላውሬል ሬይድ፤ እኔ ባለሁበት አገር ስለ መስቀል ደመራ በዓል ብዙ አይታወቅም፤ እዚህ ተገኝቼ በማክበሬና ታሪካዊ ዳራውን በማወቄ ትልቅ ኩራትና ክብር ይሰማኛል ብለዋል። "እንዲህ ዓይነት ልዩ አጋጣሚ በሕይወት ዘመን አንዴም ቢሆን ልትታደምበት የሚገባ ሁነት ነው" ሲሉ ገልጸዋል። ከቻይና የመጣችው ሌላዋ ታዳሚ ወጣት ሊዩ ኪን፤ በበዓሉ ላይ ስትገኝ የመጀመሪያዋ መሆኑን ገልጻ የበዓሉ አከባበር የሚደንቅና ልዩ ገጽታን የተላበሰ መሆኑን ተናግራለች። በበዓሉ ላይ አከባበሩ፣ ባህላዊ አልባሳትና እንቅስቃሴዎች ሁሉ አስደንቀውኛል በማለት ገልፃለች። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ከሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ለመጀመሪያ ጊዜ የመጡ 22 ሩሲያዊያን አገልጋዮችም ተሳትፈዋል።
የኢትዮጵያን ባህላዊና ኃይማኖታዊ እሴቶች በመጠበቅ ለትውልድ የማስተላለፍ የጋራ አደራና ሃላፊነት አለብን - አርበኞች
Sep 28, 2023 74
አዲስ አበባ፣ መስከረም 17/2016 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ባህላዊና ኃይማኖታዊ እሴቶች በመጠበቅ ለትውልድ የማስተላለፍ የጋራ ኃላፊነትና ታሪካዊ አደራችንን መወጣት አለብን ሲሉ አርበኞች ገለጹ። በክርስትና እምነት ተከታዮች ዘንድ ከፍተኛ ስፍራ የሚሰጠው የመስቀል ደመራ በዓል በተለያዩ የሀገሪቷ አካባቢዎች በርካታ ታዳሚዎችና ቱሪስቶች በተገኙበት በደማቅ ሥነ-ስርዓት ተከብሯል። በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይም ፕሬዚዳንት ሳኅለወርቅ ዘውዴን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ምእመናን እና በርካታ ቱሪስቶች በተገኙበት ተከብሮ ውሏል። በከብረ በዓሉ ላይ ከተገኙት መካከል ኢዜአ ያነጋገራቸው አባት አርበኛ ሻለቃ ሳሙኤል ለገሰ፤ የኢትዮጵያ ባህላዊና ሃይማኖታዊ ትውፊቶችን ከአገር አልፎ ዓለም እያወቃቸው መጥቷል ይላሉ። ለዚህም የመስቀል በዓልን ጨምሮ ሌሎችም እሴቶች በዓለም ቅርስነት ተመዘግበው እውቅናቸው እያደገ መምጣቱን ገልጸዋል። በመሆኑም የኢትዮጵያን ባህላዊና ኃይማኖታዊ እሴቶች በመጠበቅ ለትውልድ የማስተላለፍ የጋራ ሃላፊነትና አደራችንን ለመወጣት መዘጋጀት አለብን ሲሉ ተናግረዋል። የአርበኛ ልጅ የሆኑት ጽጌ ደምሴ እና ይድነቃቸው ባንታይሙሉ፤ የኢትዮጵዊያን የአንድነት መገለጫ የሆኑ ባህላዊና ኃይማኖታዊ እሴቶችን መጠበቅ የሁላችንም ሃላፊነት ነው ብለዋል። በመሆኑም እነዚህን ሃብቶች ጠብቆ ለትውልድ ለማስተላለፍ በተለይም የኃይማኖት አባቶች፣ ቤተሰብና ትምህርት ቤቶች አጠቃላይ ህብረተሰቡ ከፍተኛ ሃላፊነት አለበት ነው ያሉት። የኢትዮጵያን ባህላዊና ኃይማኖታዊ እሴቶች ጠብቆ የማስቀጠል ታሪካዊ ሃላፊነትና አደራ ሁላችንም አለብን ሲሉ ተናግረዋል። የመስቀል በዓል የአንድነት፣ የሰላምና የፍቅር መገለጫ ጭምር በመሆኑ በተለይም ወጣቶች ይህንን መልካም እሴት ይዘው መቀጠል አለባቸው ብለዋል። ከኢትዮጵያም አልፎ የዓለም ቅርስ በመሆኑ መጠበቅና መንከባከብ አለብን ሲሉ አርበኞቹ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል። የኢትዮጵዊያን ቱባ ባህላዊና ኃይማኖታዊ ትውፊቶች ተጠብቀው እንዲቀጥሉ የማስማርና ትውልድን የማነጽ ስራም በዘላቂነት መከናወን አለበት ብለዋል። ኢትዮጵያ በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) ያስመዘገበቻቸው ታሪካዊ፣ ባህላዊ፣ ሐይማኖታዊ እንዲሁም ተፈጥሯዊ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርሶች 11 መድረሳቸው ይታወቃል።
በከተማችን ባሉ የምገባ ማዕከላት ከ35 ሺህ በላይ ወገኖቻችን አገልግሎት እያገኙ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Sep 28, 2023 116
አዲስ አበባ፣ መስከረም 17/2016 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ባሉ 20 የምገባ ማዕከላት ከ35 ሺህ በላይ ወገኖች አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለፁ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ 20ኛውን የአዲስ አበባ ከተማ የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከልን ዛሬ መርቀው አገልግሎት አስጀምረዋል፡፡ በዚህም የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ባሰፈሩት መረጃ የምገባ ማዕከሉ በጉለሌ ክፍለ ከተማ በተለምዶ ቀጨኔ መድሃኒያለም በሚባለው አካባቢ መገንባቱን ጠቅሰዋል። ማዕከሉ ከ500 በላይ ለሚሆኑ የአካባቢው አቅመደካማ ነዋሪዎች በቀን አንድ ጊዜ የተመጣጠነ ምግብ የሚያቀርብ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የምገባ ማዕከሉን በ47 ሚሊየን ብር ለገነባው ቶኩማ ስታር ቢዝነስ ግሩፕ እንዲሁም ተገልጋዮቹን በቋሚነት ለመመገብ ማዕከሉን ለተረከበው የብዙአየሁ ታደለ ፋውንዴሽ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ ከንቲባዋ አጠቃላይ በከተማዋ ባሉ 20 የምገባ ማዕከላት ከ35 ሺህ በላይ ወገኖች አገልግሎት እያገኙ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡
የሽናሻ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ "ጋሪ ዎሮ" በዓል በአሶሳ ከተማ እየተከበረ ነው
Sep 28, 2023 56
አሶሳ ፤መስከረም 17/2016 (ኢዜአ):- የሽናሻ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ "ጋሪ ዎሮ" በዓል በአሶሳ ከተማ እየተከበረ ነው። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከሚከበሩት ዓመታዊ በዓላት መካከል የሽናሻ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ በዓል "ጋሪ ዎሮ" አንዱ ነው። በዓሉ በየዓመቱ መስከረም ወር አጋማሽ ላይ የሚከበር ሲሆን በዓሉን ለመታደም በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የሚኖሩ የብሔረሰቡ ተወላጆች ይሰባሰባሉ። በዓሉ ዛሬ በአሶሳ መከበር የጀመረው በብሔረሰቡ ታላላቅ አባቶች ባደረጉት የምርቃ ሥነ-ስርዓት ነው። የብሔረሰቡ የሀገር ሽማግሌ አቶ ለማ አልጋ ለኢዜአ እንደገለፁት፣ በዓሉ የብሔረሰቡ አባላት ወደ አዲስ ዓመት በመሸጋገራቸው ለፈጣሪያቸው ምስጋና የሚያቀርቡበት ነው። የበዓሉ አከባበር በሀገር ሽማግሌዎች ምርቃት የሚጀመር ሲሆን በእዚህም አዲስ የለማ ሰብል በረከት እንዲኖረው ከመመኘት በተጨማሪ ዓመቱ እንደአገር ሰላምና ደህንነት የሰፈነበት እንዲሆን ያለመ መሆኑን አስረድተዋል። በእዚህም የአገር ሽማግሌዎቹ ለአዲሱ ዓመት እንኳን አደረሳችሁ፤ ዘመኑ የሰላምና የፍቅር ይሁንላችሁ እያሉ ይመርቃሉ ብለዋል። በበዓሉ መክፈቻ ላይ ከምርቃት ጎንለጎን ደመራ የመለኮስ ሥነ-ስርዓት መካሄዱ ተጠቅሷል። በበዓሉ እለት ብሔረሰቡን የሚገልጹ የተለያዩ ባህላዊ ምግቦችም እንደሚቀርቡ ታውቋል። አቶ ለማ እንዳሉት በዓሉ ከመከበሩ አስቀድሞ በሽናሻ ብሔረሰቡ ባህል መሰረት የተጣሉ እንዲታረቁ እና ፍቅር እንዲያወርዱ ይደረጋል። በእዚህም በብሔረሰቡ ዘንድ ትልቅ ስፍራ የሚሰጠው የጋሪ ዎሮ በዓል የእርቅና የአንድነት በዓል በመባልም እንደሚታወቅ ተናግረዋል። እንደ አቶ ለማ ገለጻ የሽናሻ ብሔረሰብ የዘመን መለወጫ "ጋሪ ዎሮ" በዓል ሲከበር የተቸገሩ ሰዎችን ከመርዳት በተጨማሪ በዓሉን በአብሮነት ማሳለፍ የባህሉ እሴቶች ናቸው። በበዓሉ የብሔረሰቡን ባህላዊ እሴቶች በመጠበቅና በማጎልበት ለትውልድ ማስተላለፍ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ የብሔረሰቡ ምሁራን እና ተወላጆች ያካተተ የፓናል ውይይት እንደሚደረግም ታውቋል። የጋሪ ዎሮ የዘመን መለወጫ በዓል በአሶሳ ከተማ ሲከበር ዘንድሮ ለ13ኛ ጊዜ ሲሆን የሽናሻ ብሔረሰብ አባላት በስፋት በሚገኙበት ገጠራማ አካባቢም ባህላዊ እሴቱን ጠብቆ በታላቅ ድምቀት እንደሚከበር ታውቋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በአዲስ አበባ 20ኛውን የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከል መርቀው ስራ አስጀመሩ
Sep 28, 2023 112
አዲስ አበባ፤ መስከረም 17/2016 (ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በአዲስ አበባ 20ኛውን የተስፋ ብርሃን የምገባ ማዕከል መርቀው ስራ አስጀመሩ። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ እና ሌሎች የአስተዳደሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ጋር በመሆን ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ ማዕከሉን የመረቁት። የአገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶችና ሌሎችም የማህበረሰብ ክፍሎች በመርሃ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል። በአዲስ አበባ በተለያዩ ክፍለ ከተሞች በተገነቡ የምገባ ማዕከላት በቀን ከ35 ሺህ በላይ ዜጎች እየተመገቡ መሆኑም ተገልጿል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በመዲናዋ ጉለሌ ክፍለ ከተማ የተገነባውን 20ኛውን የምገባ ማዕከል መርቀው በይፋ ስራ ያስጀመሩ ሲሆን በወቅቱም ለአቅመ ደካሞች ማእድ አጋርተዋል።
ህዝበ ክርስቲያኑ የመስቀል በዓልን ሲያከብር ሰላምና አብሮነትን በሚያጠናክር መልኩ ሊሆን ይገባል - የእምነቱ አባቶች
Sep 28, 2023 131
አርባ ምንጭ/ሆሳዕና መስከረም 17/2016 (ኢዜአ)፦ ህዝበ ክርስቲያኑ የመስቀልን በዓል ሲያከብር ሰላምንና አብሮነትን በሚያጠናክር መልኩ ሊሆን እንደሚገባ የእምነቱ አባቶች አመለከቱ። የመስቀል በዓል ከዋዜማው ከደመራ በዓል ጀምሮ በአርባ ምንጭ ከተማና አካባቢዋ እንዲሁም በሆሳዕና በተለያዩ ሃይማኖታዊ ኩነቶች በታላቅ ድምቀት እየተከበረ ነው። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የጋሞ እና የጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የሲኖዶሱ አባል ብፁዕ አቡነ ኤሊያስ ባስተላለፉት መልዕክት ህዝበ ክርስቲያኑ የመስቀልና የደመራን ተምሳሌት በመከተል አንድነቱንና አብሮነቱን ማስጠበቅ ይገባዋል። በመከባበር፣ በመፈቃቀርና በአብሮነት በመታነጽ ከፈጣሪ ጋር ያለውን ግንኙነት ሊያጠናክር እንደሚገባም አመልክተዋል። እግዚአብሔር በመስቀሉ ስለ እኛ ነፍሱን አሳልፎ እንደሰጠ ሁሉ እኛም እርስ በርስ በርህራሄና በፍቅር ልንኖር ይገባል ሲሉም መልዕክት አስተላልፈዋል ብፁዕነታቸው። ህዝበ ክርስቲያኑ የመስቀል በአልን ሲያከብር በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኙ ወገኖች ካለው በማካፈልና በአብሮነት በሰላም፣ በመተሳሰብ መሆን እንዳለበትም አሳስበዋል። በተመሳሳይ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የሀድያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ዋና ስራ አስኪያጅ መላከ ህይወት ቀሲስ ንጉሴ ባወቀ ምዕመኑ በዓሉን ሲያከብር የአንድነት ማሳሪያ የሆነውን ፍቅርና ርህራሄ በመላበስና የመስቀልን መርህ በመከተል መሆን እንደሚገባ ተናግረዋል። እንዲሁም አቅመ ደካሞችን በመደገፍ፣ የታረዙትን በማልበስ፣ ህሙማንን በመጠየቅና አብሮ በመሆን በደስታ ማሳለፍ እንደሚገባም ገልፀዋል፡፡ በዓሉን አስመልክተው አስተያየታቸውን የሰጡት ምዕመናንና የበዓሉ ታዳሚዎች እኛ በተሰጠን ፀጋ ስናከብር የእለት ጉርስ ለማግኘት የሚቸገሩ፣ ረዳት የሌላቸው፣ በእርጅናና በህመም ምክንያት ቤት ያሉ ወገኖቻችን በማስታወስ መደገፍ ከፈጣሪም ዘንድ በረከት ያስገኛል ብለዋል። የሆሳዕና ከተማ ነዋሪው ዲያቆን ረቂቅ ፀጋዬ የአውደ ዓመት በዓላት በተለያየ መንገድ ተራርቀው የነበሩ ሰዎች ከያሉበት አካባቢ በመሰባሰብ የሚያከብሯቸውና የደስታ ጊዜን የሚያሳልፉባቸው ስለመሆናቸው ይናገራሉ። በዓሉን በአካባቢያቸው ከሚገኙ አቅመ ደካማ ወገኖች ጋር ለማሳለፍ መዘጋጀታቸውንም አስረድተዋል። ተነፋፍቆ የቆየ ቤተሰብ በጋራ በመሰባሰብ በፍቅርና በደስታ ታጅቦ ከሚከበሩ በዓላት መካከል አንዱ የመስቀል በዓል ስለመሆኑ የተናገሩት ሌላኛዋ የሆሳዕና ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ እመቤት ንጉሴ ናቸው ። የመስቀል በዓል አምላክ ለፍቅር ሲል የከፈለውን መስዋዕትነትና ትዕግስት የሚያስተምር መሆኑን አንስተው ይህን የህይወት ልምምድ በማድረግ ከሌሎች ጋር በሰላም ለመኖር እንደሚተጉ ተናግረዋል ። የመስቀል ደመራ በዓል በመላው ኢትዮጵያ የኦሮቶዶክስ ሃይማኖት ተከታዮች ዘንድ በተለያዩ ሀይማኖታዊ ክዋኔዎች በደማቅ ስነ ስርአት እየተከበረ ይገኛል።