ማህበራዊ
የአካባቢያቸውን ሰላም  በማስጠበቅ ልማትን ለማፋጠን የድርሻቸውን እንደሚወጡ  የደብረብርሀን ከተማ ወጣቶች  አስታወቁ
Apr 23, 2024 74
ደብረ ብርሀን፤ ሚያዝያ 15/2016 (ኢዜአ)፦ የአካባቢያቸውን ሰላም በዘላቂነት በማስጠበቅ የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ለማፋጠን የድርሻቸውን እንደሚወጡ የደብረ ብርሀን ከተማ ወጣቶች አስታወቁ። በከተማዋ ወቅታዊ ሰላምና ልማት በሚጠናከርበት ዙሪያ የሚመክር የወጣቶች መድረክ ዛሬ በደብረ ብርሃን ከተማ ተካሄዷል።   የመድረኩ ተሳታፊ ወጣት ትዕግስት ፍቅረ እንዳለችው ለአካባቢ ሰላም መጠበቅና ልማት መጠናከር የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ነው። ''እኛ ወጣቶች ገንቢና ምክንያታዊ አስተሳሰቦችን በማጎልበት በከተማዋ የተጀመሩ የልማት ስራዎች ዳር እንዲደርሱ ያላሰለሰ ጥረት እናደርጋለን'' ስትል ገልጻለች። በየደረጃው የሚገኙ የመንግስት አካላት አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ፈጣንና ቀልጣፋ ማድረግ እንዳለባቸው ጠቁማለች። አሁን ላይ የከተማ አስተዳደሩ የሚያከናውናቸው የልማት ስራዎች የነዋሪዎችን ህይወት ለመቀየር የሚያግዙ መሆናቸውን ጠቅሳለች።   ከወጣቶች ጋር የሚካሄዱ ውይይቶችን አጠናክሮ በማስቀጠል ምክንያታዊ አስተሳሰብ በማስቀደም የአካባቢ ሰላም አስጠብቆ በዘላቂነት ለማስቀጠል የበኩሉን እንደሚወጣ የገለጸው ደግሞ ሌላው ወጣት ደምሴ ምሳወይ ነው። በከተማው እያደገ ያለውን የንግድና የኢንቨስትመንት እንቅስቃሴ የበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የሚደግፍ መሆኑን አስታውቋል። የእምየ ምሊኒክ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ሰራዊት በዛ በበኩላቸው የከተማዋን ሰላምና ልማት አጠናክሮ ለማስቀጠል ወጣቶች በሚያከናውኗቸው ስራዎች አበረታች ለውጥ እየመጣ ነው ብለዋል። ወጣቶች ተደራጅተው የአካባቢያቸውን ሰላም በማስጠበቅ የልማት ስራዎች ሳይደናቀፉ እንዲቀጥሉ በማድረግ የጎላ ሚና መወጣታቸውን አመልክተዋል።   የከተማ አስተዳደሩ ከንቲባ የወጣቶች ዘርፍ አማካሪ አቶ ኃይለማሪያም ወንድም እሸት የወጣቶችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የወጣቶችን የስራ አጥነት ችግር ለመፍታት በኢንተርፕራይዞች በማደራጀት ከ9 ሺህ ለሚበልጡ ወጣቶች የስራ አድል በመፍጠር ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። የወጣቶችን የላቀ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አመልክተው ወጣቶች ለአካባቢያቸው ሰላም በጋራ መስራትን መቀጠል እንዳለባቸው መልዕክት አስተላልፈዋል። በምክክር መድረኩ ከደብረብርሃን የተለያዩ ክፍለ ከተሞች የተውጣጡ ወጣቶችና በየደረጃው ያሉ የከተማ አስተዳደሩ አመራር አባላት ተሳትፈዋል።      
የከተማውን ሰላም በዘላቂነት ለማስጠበቅ ተሳትፎአቸውን እንደሚያጠናክሩ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ
Apr 23, 2024 77
ጎንደር ፤ ሚያዚያ 15 /2016 (ኢዜአ)፡- በጎንደር ከተማ በብሎክ አደረጃጀት ታቅፈው የአካባቢአቸውን ሰላምና ደህንነት በዘላቂነት ለማስጠበቅ እያደረጉት ያለውን ተሳትፎ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ። በከተማው የሰፈነውን ሰላም አጠናክሮ በማስቀጠል ዙሪያ የከተማው አስተዳደሩ ከህዝቡ የተወከሉ ነዋሪዎች ጋር ዛሬ ምክክር አድርጓል፡፡ ከተሳታፊዎቹ መካከል አቶ መስፍን ጌታነህ እንዳመለከቱት የብሎክ አደረጃጀቱ ነዋሪው አካባቢውን ከወንጀል ፈጻሚዎች ነቅቶ በመጠበቅ ሰላሙን እንዲያረጋግጥ አግዟል፡፡ የብሎክ አደረጃጀቱ "በመኖሪያ አካባቢያችን ይፈጸሙ የነበሩ ስርቆትና የመሰረተ ልማት ዝርፊያዎችን ማስቀረት አስችሏል" ብለዋል፡፡ ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ዘውዱ መንግስቴ በበኩላቸው የብሎክ አደረጃጀቱ በባጃጅ ይፈጸሙ የነበሩ ስርቆቶች መቆጣጠር ከማስቻሉም በላይ ወንጀል ፈጻሚዎችን ለህግ ለማቅረብ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡ ተደራጅተው በሚያከናውኑት ጥበቃ "ከዚህ በፊት ይፈጸሙ የነበሩ የንግድ ቤቶች ዝርፊያና የሰው እገታ ወንጀሎች እየቀነሱ መጥቷል" ያሉት ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ገብሬ ዳኘው ናቸው፡፡ የብሎክ አደረጃጀቱ ህዝቡ ከመንግስት የፀጥታ መዋቅር ጋር በመቀናጀት ለከተማው ዘላቂ ሰላም መረጋገጥ የሚያደርገውን ጥረት እያገዘ በመሆኑም አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል።   የአዘዞ ክፍለ ከተማ አመራር አባል አቶ ሙሉጌታ አወቀ በበኩላቸው ህዝቡ በብሎክ ተደራጅቶ ባደረገው ተሳትፎ ሁለት የኤሌትሪክ ትራንስፎርመሮችን ከዝርፊያ በማዳንና ወንጀለኞችን በመያዝ ለህግ ማቅረብ መቻሉ ተናግረዋል፡፡ በከተማ አስተዳደሩ የከንቲባው የህዝብ ግንኙነትና አደረጃጀት አማካሪ አቶ ቻላቸው ዳኘው የከተማው ነዋሪዎች በ91 ቀጣናዎችና በ633 ብሎኮች ተደራጅቶ የአካባቢውን ሰላም እየጠበቁ እንደሚገኙ ገልጸዋል። መንግስት ሰላሙን ለማጽናት እያደረገ ያለውን ጥረት በማገዝ በኩል የህዝቡ ተሳትፎ አበረታች መሆኑን ጠቅሰው፤ "ተሳትፎው ተጠናክሮ እንዲቀጥልም ከተማ አስተዳደሩ እየደገፈ ይገኛል" ብለዋል፡፡ የአማራ ክልል ስራ አመራር አካዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት ዶክተር ሰብስበው አጥቃው በበኩላቸው የከተማው ህዝብ የሰላሙ ባለቤት በመሆን እያደረገ ያለው ተሳትፎ ለሌሎች አካባቢዎች አርአያነት ያለው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በምክክር መድረኩ በከተማው ከሚገኙ ስድስት ክፍለ ከተሞች የተውጣጡ የአገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ የንግዱ ማህበረሰብ አባላትና የአመራራ አባላት ተሳታፊ ሆነዋል።      
በኢትዮጵያ የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ትምህርት የሚወሰድባቸው ናቸው 
Apr 23, 2024 49
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2016 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ትምህርት የሚወሰድባቸው ናቸው ሲሉ የደቡብ ሱዳን የሥርዓተ ጾታ፣ የሕፃናት እና የማህበራዊ ደህንነት ሚኒስትር አያ ዋሪሌይ ገለጹ። በደቡብ ሱዳን የሥርዓተ-ፆታ እና የማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ልኡካን ቡድን ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተመራጭ የሴቶች ኮከስ አባላት ጋር የልምድ ልውውጥ አድርጓል። በልምድ ልውውጥ መድረኩም በኢትዮጵያ የሴቶችን ተጠቃሚነት እና ተሳትፎ ለማሳደግ የፓርላማ ተመራጭ ሴቶች ኮከስ እያከናወናቸው ያሉ ተግባራትን የሚመለከት ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡ የደቡብ ሱዳን የሥርዓተ ጾታ፣ የሕፃናት እና የማህበራዊ ደህንነት ሚኒስትር አያ ዋሪሌይ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ በደቡብ ሱዳን ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን የበኩሏን ሚና እየተወጣች መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዚህም ደቡብ ሱዳናውያን ኢትዮጵያን እንደ ሁለተኛ ቤታቸው እንደሚቆጥሯት ተናግረዋል፡፡ የልዑክ ቡድኑ ጉብኝት በኢትዮጵያ ሴቶች በተለይ በፖለቲካው መስክ ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ እየተከናወኑ ባሉ ስራዎች ላይ ልምድ ለመውሰድ ያለመ ነው ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች የሚበረታቱና ትምህርት የሚወሰድባቸው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ደቡብ ሱዳንም ከሰላም ስምምነቱ ወዲህ ሴቶችን ለማብቃት የሚያስችል ልዩ ድጋፍ ቀርጻ ተግባራዊ እያደረገች መሆኑን አብራርተዋል፡፡ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተመራጭ ሴቶች ኮከስ ሰብሳቢ ኪሚያ ጁንዲ በበኩላቸው ምክር ቤቱ የሴቶችን ማህበራዊ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማሳደግ እያሰራቸው ያሉ ስራዎችን በሚመለከት ለልዑክ ቡድኑ ገለጻ ተደርጓል ነው ያሉት፡፡ የፓርላማ ተመራጭ ሴቶች ኮከስ ህጎች ሲወጡ እንዲሁም የአስፈጻሚ አካላት የክትትልና ቁጥጥር ስራዎች ሲከናወኑ የሴቶችን ተሳትፎ እንዲጎለብት በትኩረት እንደሚሰራም አውስተዋል፡፡ የሴቶችን ፖለቲካዊ ተሳትፎ ለማሳደግ እንደ ሀገር በተሰራው ስራም በምክር ቤት ውስጥ የሴቶች ተሳትፎ እያደገ መምጣቱንም ጨምረው ተናግርዋል፡፡ በምክር ቤቱ የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር ፈትሂ ማህዲ ኢትዮጵያ እና ደቡብ ሱዳን ጠንካራ ወዳጅነት ያላቸው አገራት መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ ኢትዮጵያ በምክር ቤት ውስጥ የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ እያከናወነች ካለው ስራ ባሻገር በዲፕሎማሲያዊ በሰላም ጉዳዮች ያላትን ተሞክሮ ለልዑክ ቡድኑ ገለጻ መደረጉንም ተናግረዋል፡፡        
በከተማው የተገነቡ ፓርኮች ምቹና አማራጭ የመዝናኛ ሥፍራዎች ሆነዋል
Apr 23, 2024 75
አዲስ አበባ ፤ሚያዝያ 15/2016 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ ያሉት ፓርኮች ለከተማዋ ውበት ከመሆን ባለፈ ለቱሪስቶች ምቹና ተመራጭ የመዝናኛ ሥፍራዎች መሆናቸውን የአገር ውስጥ ጎብኝዎች ተናገሩ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በጥቂት ዓመታት ተገንብተው ለአገልግሎት ክፍት የሆኑ ፓርኮች ከቱሪስት መዳረሻነትም ባለፈ የከተማዋ የውበት መገለጫ ሆነው በማገልገል ላይ ይገኛሉ።   በአጭር ጊዜ ውስጥ ግንባታቸው ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት የሆኑት የአንድነት፣ የእንጦጦ እና ሸገር ፓርኮች እንዲሁም የወዳጅነት አደባባይ ለዚህ ሁነኛ ማሳያዎች ናቸው። ኢዜአ ያነጋገራቸው ጎብኝዎች ፓርኮቹ የአዲስ አበባን ገፅታ ያስዋቡና ለመዝናኛነት የምንመርጣቸው ዓይነተኛ ሥፍራዎች ሆነዋል ብለዋል።   ፓርኮቹን ሲጎበኙ ካገኘናቸው መካከል አቶ ማንደፍሮ አሰፋ እና ወይዘሮ ሰላማዊት ሙሉጌታ በተለይ አንድነት ፓርክ ታሪካዊ እና ተፈጥሯዊ መስህቦቹ በአንድ ላይ በመያዙ በርካታ ነገሮች ማየት ያስችላል ብለዋል። በተለይ ለትራንስፖርት አመቺ በሆነ ሥፍራ መገንባቱ ብዙ ድካም ሳይኖር በቀላሉ ተዝናንቶ ለመመለስ ጥሩ ዕድል የፈጠረ መሆኑን ገልፀዋል።   በአዲስ አበባም ሆነ በአገሪቱ እየተሰሩ ያሉት ፓርኮች የአገሪቱን ቱሪዝም በማነቃቃትና ሰዎችም ምቹ የመዝናኛ ሥፍራ እንዲያገኙ እያደረገ መሆኑን ጠቁመዋል። ፓርኮቹ በቂ የመኪና ማቆሚያና ከከተማው ያልራቁ በመሆኑ በቅርበት እንዲዝናኑና በቀላሉ መንፈሳቸውን ለማደስ ዕድል እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል።   በተለይ በአዲስ አበባ መሃል እንዲህ ዓይነት ፓርኮች መሰራታቸው በሥራ ጫና የደከመ አእምሮን ዘና ለማድረግ ጥሩ አጋጣሚ የሚፈጥር መሆኑን ወይዘሮ ቃልኪዳን ኃይለማሪያም፣ ወይዘሪት ስምረት ፍስሐ እና አቶ ንጉሴ ለማ ገልፀዋል። በኢትዮጵያ የተለያዩ ቦታዎች እምቅ ኃብቶችንና እሴቶችን እየተመለከቱ መዝናናት መቻል ትልቅ ዕድል መሆኑንም ተናግረዋል።   በዚህም ከተጣበበ ጊዜ የተነሳ ለመዝናናት ላልቻሉ ዜጎች ጥሩ ሁኔታ መፈጠሩን ገልጸው በፓርኩ ህጻናት ልጆችን ይዘው በአነስተኛ ዋጋ መዝናናት እንዳስቻላቸውም ተናግረዋል።   ከወላጆቻቸው ጋር ለመዝናናት የመጡ ህፃናት በበኩላቸው፤ በፓርኮቹ ባዩት ነገሮች መደሰታቸውን ገልፀዋል። የአንድነት ፓርክ ከፍተኛ የኮሙኒኬሽን ባለሙያ ጌታቸው በየነ በበኩላቸው፤ አሁን ላይ ፓርኩ በቀን በርካታ ጎብኝዎችን በማስተናገድ ላይ ይገኛል ብለዋል። ፓርኮቹ የጉብኝት ባህል እንዲያድግና የአገር ውስጥም ሆነ የውጭ ጉብኝዎች ቁጥር እንዲያድግ ከፍተኛ አስተዋፅዖ እያበረከቱ መሆኑን ገልፀዋል። በመዲናዋ የተገነቡት ፓርኮች የከተማዋን ውበት ከመጨመር ባለፈ ለአገር ውስጥና ለውጭ አገር ጎብኝዎች ሁነኛ የመዝናኛ ሥፍራ መሆናቸውን ተናግረዋል። የአንድነት ፓርክ፣ እንጦጦ ፓርክ እና ወዳጅነት አደባባይ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት በአጭር ጊዜ ውስጥ ተገንብተው ለቱሪስቶች ክፍት የተደረጉ ውብና አስደናቂ ሥፍራዎች መሆናቸው ይታወቃል።        
የአፍሪካ ከተሞች ፎረም በመጭው መስከረም በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ አስታወቁ
Apr 23, 2024 91
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 15/2016(ኢዜአ)፡- የአፍሪካ ከተሞች ፎረም በመጪው መስከረም በአዲስ አበባ እንደሚካሄድ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ አስታወቁ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ "ዘላቂ የክትመት ምጣኔ ለአፍሪካ ትራንስፎርሜሽን - አጀንዳ 2063" በሚል መሪ ቃል የአፍሪካ ከተሞች ፎረም በመጭው መስከረም በአዲስ አበባ ይካሄዳል ብለዋል። ዛሬ የአፍሪካ ከተሞች ፎረም ብሄራዊ አስተባባሪ አብይ ኮሚቴ የመክፈቻና የግንዛቤ መስጫ መድረክ መካሄዱንም ጨምረው ገልጸዋል። ኢትዮጵያ እንደ ሀገር ታሪካዊት፣ የተባበሩት መንግስታት እና የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የአሁኑ አፍሪካ ህብረት መስራች ሀገር ይህንን ከአንድ ሺህ አምስት መቶ በላይ ተሳታፊዎች እንደሚታደሙበት እንደሚጠበቅም ጠቁመዋል። በመሆኑንም ኢትዮጵያ የአፍሪካ ወንድማማቾች መመካከሪያ መድረክ ለማዘጋጀት የተሰጣትን አፍሪካዊ ኃላፊነት በሚገባ ለመወጣት ዝግጁ መሆኗን በመድረኩ ተግባብተናል ብለዋል።
የህዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Apr 23, 2024 72
ድሬዳዋ፤ሚያዝያ 15/2016 (ኢዜአ) ፦ የህዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች ለማቃለል እየተሰሩ የሚገኙ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር ተናገሩ። የአስተዳደሩ ያለፉት ዘጠኝ ወራት የሴክተር ተቋማትና ማዘጋጃ ቤት አገልግሎት ዘርፎች የስራ አፈፃጸም ሪፖርት እየተገመገመ ነው። በዚህም በማህበራዊ፣ በምጣኔ ሀብትና በመልካም አስተዳደር የተከናወኑ ስራዎች በትኩረት እየተፈተሹ መሆናቸውም ታውቋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት፤ በዘንድሮው በጀት ዓመት በገጠርና በከተማ የተከናወኑ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች አበረታች ለውጦች እያመጡ ናቸው። በተለይም ስራ አጥነት ችግር ለመፍታት፣ ለነዋሪዎች ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት፣ ገቢን አሟጦ ለመሰብሰብና የገጠሩን ህብረተሰብ የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የተከናወኑ ተግባራት አበረታች ናቸው ብለዋል። እነዚህን ለውጦች በላቀ ደረጃ ለማሳደግ በየደረጃው የሚገኘው አመራር ሌት ተቀን ርብርቡን አጠናክሮ መቀጠል እንደሚገባው ነው ያሳሰቡት። በተመሳሳይ ተላላፊ በሽታዎችን የመከላከልና ከተማዋን ውብና ፅዱ ለማድረግ የተከናወኑ የማህበራዊ ዘርፍ ተግባራት በተቀናጀ መንገድ ተጠናክረው ይቀጥላሉ ብለዋል።   የአስተዳደሩ ምክትል ከንቲባ ሀርቢ ቡህ በበኩላቸው በየተቋማቱ የተጀመሩ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት የመስጠት ሂደቶችን በማጠናከር የህዝብ ጥያቄዎች በፍጥነትና በጥራት የመመለስ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። በበጀት አመቱ 124 ነባርና አዳዲስ የልማትና መልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን የሚያቃልሉ ፕሮጀክቶች በመተግበር ላይ መሆናቸውን የተናገሩት ደግሞ የድሬዳዋ አስተዳደር የፕላንና ኢኮኖሚ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ኃይለማርያም ዳዲ ናቸው። ከእነዚህ የልማት ፕሮጀክቶች መካከል አስራ ሁለቱ ተጠናቀው አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል፤ ሰባቱ ደግሞ በመጠናቀቅ ላይ ናቸው ብለዋል። እንደ አቶ ኃይለማሪያም ገለፃ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ ለመሰብሰብ በተከናወኑ ተግባራትም ከሦስት ቢሊዮን 234 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ በማገኘት የዕቅዱ 85 በመቶ ተሳክቷል። ከመዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች ለማግኘት የታሰበውን ገቢ በቀሪ ወራት ለመሰብሰብ መረባረብ እንደሚገባ በማከል። የግምገማው መድረክ እንደቀጠለ ሲሆን የአስተዳደሩ የአመራር አባላት ተሳታፊ ሆነዋል።    
በኢትዮጵያ በምርምር ላይ የሚገኘው የካላዛር ህክምና መድሃኒት ወደ ምዕራፍ ሁለት ክሊኒካል ሙከራ ደረጃ ተሸጋገረ
Apr 23, 2024 87
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 15/2016 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ በምርምር ላይ የሚገኘው የካላዛር ህክምና መድሃኒት ወደ ምዕራፍ ሁለት ክሊኒካል ሙከራ ደረጃ መሸጋገሩን ፈውስ ትኩረት ለተነፈጋቸው በሽታዎች ኢኒሼቲቭ አስታወቀ። በምርምር ላይ ያለው የካላዛር መድሃኒት በአፍ የሚወሰድ ሲሆን በምስራቅ አፍሪካ በሽታውን ለማጥፋት የተያዘው ግብ እውን እንዲሆን ያግዛል ተብሏል። በሳይንሳዊ ስሙ ''ቬሴራል ሊስማናሊስ'' በተለምዶ ካላዛር የሚባለው በሽታ በአሸዋ ዝንብ ንክሻ የሚተላለፍ ሲሆን በምስራቅ አፍሪካ፣ ደቡብ እስያና ደቡብ አሜሪካ በሚገኙ 80 አገራት እንደሚገኝ መረጃዎች ያመለክታሉ። በሽታው በተለይም ሞቃታማ በሆኑ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ላይ በስፋት ይከሰታል። በጎንደር ዩኒቨርሲቲ የካላዛር በሽታ ጥናትና ህክምና ማዕከል ዳይሬክተር ሳሙኤል ተሾመ (ዶ/ር) በኢትዮጵያ የካላዛር በሽታ የመጨመር አዝማሚያ በማሳየቱ ለበሽታው ፈዋሽና አስተማማኝ መድሃኒት ለማግኘት የሚደረገው ምርምር ወደ ምዕራፍ ሁለት መሸጋገሩ ተስፋ የሚሰጥ ነው ብለዋል። ምርምሩ መድሃኒት ሆኖ ለታማሚው ለመድረስ ከዚህ በኋላ ሁለት ደረጃዎችን ማለፍ እንደሚጠበቅበት ገልጸው፣ ውጤታማና ደህንነቱ የተጠበቀ ህክምና የማስገኘት እድሉ ሰፊ መሆኑንም ተናግረዋል። ምርምሩን ኢትዮጵያውያን ከተለያዩ አገራት ተመራማሪዎችና የላቦራቶሪ ተቋማት ጋር በጋራ እያከናወኑት መሆኑንም አስረድተዋል። በአፍሪካ አሁን ላይ የካላዛር ህክምና ለ17 ቀን በመርፌ የሚሰጥ ሲሆን የተለያዩ የጎንዮሽ ጉዳቶች እንዳሉት አመልክተዋል። በኢትዮጵያ የመድሃኒት ሙከራ ምርምር መስፈርት መሰረት እየተካሄደ ያለው አዲሱ የ“LXE408” መድሃኒት በአፍ የሚወሰድ ሲሆን መድሃኒቱ አሁን ከሚሰጠው ህክምና የበለጠ ፈዋሽና አስተማማኝ እንደሚሆን ይጠበቃል ብለዋል። አሁን ላይ በኢትዮጵያ ያሉት የካላዛር ህክምና አማራጮች ውስንነት ያለባቸው መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ ህሙማን የህክምና አገልግሎት ለማግኘት ረጅም ርቀት መጓዝና ሆስፒታል ውስጥ ተኝተው መታከም ግዴታ እንደሚሆንባቸው አመልክተዋል። በምርምር ላይ የሚገኘው ህክምና ፈዋሽ፣ የጎንዮሽ ጉዳቱ አነስተኛ፣ ህሙማን ደግሞ በመኖሪያ ቤታቸው አቅራቢያ በሚገኙ የመጀመሪያ ደረጃ የጤና ተቋማት ህክምናውን በቀላሉ ማግኘት እንዲችሉ የሚያግዝ እንደሚሆን ይጠበቃል ነው ያሉት። በአለም ጤና ድርጅት ተመራማሪና የካላዛር በሽታ መከላከል ተጠሪ ሳዉራብ ጃይን (ዶ/ር) እኤአ በ2030 ለህብረተሰብ ጤና ጠንቅ የሆኑትንና ትኩረት የተነፈጉ የትሮፒካል በሽታዎች በዋናነትም ካላዛርን ለማጥፋት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህ ደግሞ አዳዲስ ምርምሮችን ማካሄድና የተሻሻሉ የህክምና ዘዴዎችን መጠቀም ወሳኝ ነው ብለዋል። የካላዛር በሽታ ትኩሳት፣ የክብደት መቀነስ፣ ከልክ ያለፈ የጣፊያና የጉበት ዕድገትን ያስከትላል። በምስራቅ አፍሪካ በየዓመቱ ከ30 አስከ 40 ሺ ሰዎች በበሽታው የሚጠቁ ሲሆን አብዛኞቹ ህሙማን በኢትዮጵያ፣ ሱዳንና ደቡብ ሱዳን አንደሚገኙ መረጃዎች ያመለክታሉ። በየአመቱ ከ50 እስከ 90ሺ ሰዎች በካላዛር የሚያዙ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ እድሜያቸው ከ15 አመት በታች የሆኑ ህጻናት ከግማሽ በላይ ናቸው ተብሏል። በኢትዮጵያ እየተካሄደ የሚገኘው ክሊኒካዊ ሙከራ የገንዘብ ድጋፉን ያገኘው ከአውሮፓና በማደግ ላይ ያሉ አገራት ክሊኒካዊ ሙከራዎች ጥምረት (EDCPT) መሆኑም ታውቋል።
ስታርት አፖች በጤናው ዘርፍ ያቀረቧቸው የቴክኖሎጂ ውጤቶች ጥራቱን የጠበቀና የተቀላጠፈ አገልግሎት መስጠት የሚያስችሉ ናቸው
Apr 23, 2024 62
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 15/2016(ኢዜአ)፦ ስታርት አፖች በጤናው ዘርፍ ያቀረቧቸው የቴክኖሎጂ ውጤቶች ጥራቱን የጠበቀና የተቀላጠፈ አገልግሎት መስጠት የሚያስችሉ መሆናቸውን በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የኢንስቲትዩት ኦፍ ፋርማሲዩቲካል ሳይንስ መምህራን ገለፁ። በስታርት አፕ አውደ ርዕይ የቀረቡት የቴክኖሎጂ ውጤቶች የአገሪቱን የቴክኖሎጂ አቅም ከመሰረቱ መቀየረ የሚያስችሉ በመሆኑ ተግባር ላይ እንዲዉሉ እገዛ ማድረግ እንደሚገባ ምሁራኑ ተናግረዋል። ከመጋቢት 30 እስከ ሚያዝያ 20 ቀን 2016 ዓ.ም የሚቆየው የኢትዮጵያ "ስታርት አፕ" አውደ-ርዕይ የመንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በሳይንስ ሙዚየም ለጎብኚዎች ክፍት መደረጉ ይታወቃል። በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በግብርና፣ በጤና፣ በትምህርት፣ በኢንዱስትሪ፣ በፋይናንስና በሌሎች ዘርፍ የተሰማሩ ጀማሪ ሥራ ፈጣሪዎች ''ስታርት አፖች'' በአውደ-ርዕዩ ስራዎቻቸውን አቅርበዋል። አውደ ርዕዩን ሲጎበኙ ኢዜአ ያነጋገራቸው የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ የኢንስቲትዩት ኦፍ ፋርማሲዩቲካል ሳይንስ መምህራን በቴክኖሎጂ ዘርፍ አቅም ያላቸውና ለቀጣዩ ትውልድ መነሳሳትን የሚፈጥሩ ስራዎችን መመልከታቸውን ተናግረዋል። በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ከኢንስቲትዩት ኦፍ ፋርማሲዩቲካል ሳይንስ መምህር ዶክተር ከተማ ታፈሰ እንዳሉት በወጣት ስታርት አፖች እየተሰሩ ያሉ ቴክኖሎጂዎች ዲጂታል ኢኮኖሚውን የሚደግፉና አገርን የሚያሳድጉ ናቸው። በጉብኝታቸው በትምህርት፣በሎጅስቲክስ፣ በህክምናና በጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ ወደ ስራ መቀየር የሚችሉ የቴክኖለጂ ስራዎችን መመልከታቸውን ተናግረዋል። በአውደ ርዕዩ ለነገ መሰረት የሚጥሉ ስራዎችን መመልከታቸውን የገለፁት ደግሞ በአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ከኢንስቲትዩት ኦፍ ፋርማሲዩቲካል ሳይንስ መምህር ዶክተር ተሾመ ደግፌ ናቸው። በተለይ በጤናው ዘርፍ የቀረቡት ቴክኖሎጂዎች ስራን የሚያቀላጥፉና ጥራትን ማረጋገጥ የሚያስችሉ መሆናቸውን ነው መምህራኑ የተናገሩት። የጤናው ዘርፍ ቴክኖሎጂ ይዘው የቀረቡ ስታርት አፖች በበኩላቸው ታካሚዎች በቤታቸው ሆነው ከህክምና ቀጠሮ ጀምሮ ህክምና እስኪያገኙ ድረስ ያለውን ሂደት የሚያሳልጠው ቴክኖሎጂ እንግልትን የሚያስቀር መሆኑን ገልፀዋል። "የርህራሄ የስኳር ህክምና ማዕከል" ማርኬቲንግ ባለሙያ ዶክተር ያኔት ዕቁባይ ማዕከሉ የስኳር ህመምን የተመለከተ ትምህርትና በጤና ባለሙያዎች የቤት ለቤት እንክብካቤና ህክምና መስጠት የሚያስችል መሆኑን ገልፃለች። "የጤናዎ " የኦፕሬሽን ዘርፍ ባለሙያ ፍሬህይወት ደመላሽ በበኩሏ በድረገፅ ፣ ሞባይል መተግበሪያና በጥሪ ማዕከል በመታገዝ ታካሚዎች ማንኛውንም ህክምና ማግኘት የሚችሉበትን ቴክኖሎጂ ይዘው መቅረባቸውን ተናግራለች። "የጤና ፈርስት ፕላስ" ማርኬቲንግ ባለሙያ ሃይማኖት ታዬ እንዳለችው ቴክኖሎጂው የቴሌ ህክምና የሚሰጥበት ሲሆን ታካሚው በድምጽና ምስል ጥሪ፣ በጤና ተቋማት በመምጣት እንዲሁም የቤት ለቤት አገልግሎት እንዲያገኝ የሚያስችል ነው። ይዘው የቀረቧቸው ቴክኖሎጂዎች የታካሚን እንግልት የሚቀንሱና የጤና ባለሙያዎች ተጨማሪ ስራን እንዲሰሩ እድል የሚፈጥር ነው። መሰል መድረኮች ስታርት አፖች ስራቸውን እንዲያስተዋውቁና ከሌሎች ስታርት አፖች ልምድ እንዲቀስሙ የሚያስችሏቸው እንደሆኑም ተናግረዋል።      
ህብረቱ የጤናውን ዘርፍ ከማጠናከር ረገድ በኢትዮጵያ እየሰራ ያለው ስራ የሚያበረታታ ነው-ዶክተር መቅደስ ዳባ
Apr 23, 2024 83
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 15/2016 (ኢዜአ)፦ የአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን የጤናውን ዘርፍ ከማጠናከር ረገድ በኢትዮጵያ እየሰራ ያለው ስራ የሚያበረታታ መሆኑን የጤና ሚኒስትሯ ዶክተር መቅደስ ዳባ ተናገሩ፡፡ ዶክተር መቅደስ ዳባ ከአውሮፓ ህብረት ኮሚሽን ጋር ተወያይተዋል። በውይይቱ ወቅት ዶክተር መቅደስ እንደገለጹት ህብረቱ የጤናውን ዘርፍ ከማጠናከር ረገድ በኢትዮጵያ እየሰራ ያለው ስራ የሚያበረታታ ነው። በቀጣይም የማይበገር የጤና ስርዓትን ከመገንባት ረገድ፣ ጾታዊ ጥቃትን ለመከላከልና አስፈላጊውን የጤና ምላሽ መስጠት፣ ስርዓተ ፆታን በጤናው ዘርፍ ለማካተት፣ የአዕምሮ ጤና አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ እየተሰሩ ያሉ ስራዎችን ህብረቱ እንዲደግፍ ጠይቀዋል። በተጨማሪም የጤና ባለሙያዎችን ማሰልጠንና ማብቃት እና በግጭት የወደሙ ጤና ተቋማትን መልሶ ከማቋቋምና ከመገንባት ረገድ እየተሰሩ ባሉ ስራዎች ላይም ህብረቱ አስፈላጊውን እገዛ እንዲያደርግም ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። በቀጣናው የላቀ የባዮ ሜዲካል ላብራቶሪን ከማስፋፋትና ከራስ አልፎ ለሌሎች ሀገራትም አቅም መሆን የሚያስችል ስራ እየተሰራ ስለሆነ ህብረቱ ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫውን በእነዚህ ጉዳዮች ላይ እንዲያደርግም ልዑካኑን አስረድተዋል። የአውሮፓ ህበረት ኮሚሽን ኃላፊ ሮበርቶ ሺሊሮ በበኩላቸው ተቋማቸው ለበርካታ ዓመታት የጤናው ዘርፍ አጋር በመሆን ዘርፍ ብዙ ስራዎችን እየሰራ እንደቆየ ገልጸዋል። የማይበገር የጤና ስርዓትን እውን ለማድረግ እና ሁለንተናዊ የጤና ሽፋንን ከማሻሻል ረገድ ተቋማቸው አስፋላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸው በህብረቱ የሚደገፉ ፕሮጀክቶን በተሳለጠ መልኩ ለማከናወንና ለውጣቸውንም በቅርበት እየተከታተሉ ለመገምገም የሚያስችል ስልት መንደፍ እንደሚገባውም ገልጸዋል። የግሉን የጤና ዘርፍ ከማብቃት እና ተሳታፊ ከማድረግ ረገድ ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ጋር በመተባበር በርካታ ስራዎችን ለመስራት ፍላጎት እንዳለው ኃላፊው ጠቅሰዋል። በግጭት ምክንያት የወደሙ ተቋማቶችን መልሶ ከመገንባት፣ ጾታዊ ጥቃት ላይ እና ስርዓት ፆታን ከማካተት እንዲሁም የጤና ባለሙያዎችን ከማብቃት ረገድ አበክረው እንደሚሰሩ ቃል መግባታቸውን ከጤና ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ሆስፒታሉ ከ1 ሺህ 500 ለሚበልጡ ሰዎች ነጻ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ቀዶ ህክምና በዘመቻ መስጠት ጀመረ
Apr 22, 2024 119
ደሴ ሚያዝያ 14/016- (ኢዜአ)፤ በደሴ ከተማ አስተዳደር የሚገኘው ቦሩ ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል ከ1 ሺህ 500 ለሚበልጡ ሰዎች ነጻ የዓይን ሞራ ግርዶሽ ቀዶ ሕክምና አገልግሎት በዘመቻ መስጠት ጀመረ። በዓይን ሞራ ግርዶሽ ለሚሰቃዩ ከ1 ሺህ 500 ለሚበልጡ ሰዎች ነጻ የቀዶ ሕክምና አገልግሎቱ መስጠት የተጀመረው ዛሬ ነው፡፡ የሆስፒታሉ ሥራ አስኪያጅ አቶ ሲሳይ ተበጀ እንደገለጹት፤ ባለድርሻ አካላትን በማስተባበር በተጀመረው የሕክምና አገልግሎት ስድስት የዘርፉ ስፔሻላይዝድ ዶክተሮችን ጨምሮ 30 የዓይን ሐኪሞች እየተሳተፉ ናቸው። ዛሬ ብቻ ከ600 ለሚበልጡ ሰዎች ሕክምና መሰጠቱን ጠቁመው፤ ከደሴ፣ ከኮምቦልቻን ጨምሮ በአካባቢው ያሉ ዜጎች በሕክምናው ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ተናግረዋል። የሕክምና አገልግሎቱ ከሚያዚያ 14 እስከ ግንቦት 19 ቀን 2016 ዓ.ም እንደሚቆይ ጠቅሰው፤ ዘመቻው በሕክምና መዳን እየቻሉ በተለያየ ምክንያት መታከም ያልቻሉና በዓይን ሞራ ግርዶሽ እየተሰቃዩ ያሉ ወገኖችን ችግር ለመፍታት የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። ህክምናውን በነፃ ከመስጠት ባሻገር የታካሚዎች የትራንስፖርት እና ሌሎች ወጭዎች እንዲሸፍኑ መደረጉን አመልክተዋል። በሆስፒታሉ የዓይን ሕክምና ክፍል ኃላፊና የዘመቻው አስተባባሪ አቶ እንዳልክ ያረጋል በበኩላቸው፤ የዓይን ሞራ ግርዶሽ በወቅቱ ካልታከመ ሙሉ በሙሉ የዓይን ብርሃንን እስከማሳጣት ይደርሳል። ዛሬ የተጀመረው ሕክምና ቀደም ብሎ ለመታከም እድሉን ያላገኙ ወገኖችን እንደሚያግዝ ገልፀዋል። በተንታ ወረዳ የቀበሌ 05 ነዋሪ ወይዘሮ ንግስት ጋሹ በሰጡት አስተያየት፤ የዓይናቸው እይታ መዳከሙን ተከትሎ በቤት ውስጥ ከዋሉ አንድ ዓመት አልፏቸዋል፡፡ ዛሬ በሆስፒታሉ ነጻ ሕክምና እንዳገኙና ሙሉ በሙሉ እይታቸው ይመለሳል የሚል ተስፋ እንዳላቸው ገልፀዋል። የዓይናቸው የማየት አቅም በመዳከሙ በቤት ውስጥ መዋል ከጀመሩ ሁለት ዓመት እንዳለፋቸው የገለፁት ደግሞ የአጅባር ከተማ ነዋሪ አቶ ይመር አሊ ናቸው። በተደረገላቸው የነፃ ህክምና መደሰታቸውን ጠቅሰው፤ በዚህም እይታቸው እንደሚመለስ ያላቸውን ተስፋ ተናግረዋል። የቦሩ ሜዳ ጠቅላላ ሆስፒታል ባለፉት አምስት ዓመታት ከ16 ሺህ ለሚበልጡ ሰዎች የዓይን ሕክምና አገልግሎት መስጠቱን ከሆስፒታሉ የተገኘ መረጃ ያመለክታል።  
የአዲስ አበባ ከተማ ፅዳት አስተዳደር ኤጀንሲ በመዲናዋ ያለውን የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ለማዘመን የሚያስችል ረቂቅ ማስተር ፕላን ይፋ አደረገ
Apr 22, 2024 128
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 14/2016 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ ፅዳት አስተዳደር ኤጀንሲ በመዲናዋ ያለውን የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ለማዘመን የሚያስችልና ለቀጣይ 20 ዓመታት የሚተገበር ረቂቅ ማስተር ፕላን ይፋ አደረገ። ኤጀንሲው ጉዳዩን በሚመለከት ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ አውደ ጥናት አካሂዷል፡፡   የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር እሸቱ ለማ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት በመዲናዋ ቆሻሻን በአግባቡና በተደራጀ መልኩ ሰብስቦ ለማስተዳደርና መልሶ ለመጠቀም ጥናትና ምርምርን መሰረት ያደረገ አሰራር መዘርጋት አስፈልጓል ነው ያሉት፡፡ በመሆኑም ጥናትን መሰረት ባደረገ መልኩ በመዲናዋ ለሚቀጥሉት 20 ዓመታት የሚተገበር የተቀናጀ የደረቅ ቆሻሻ አስተዳደር ረቂቅ ማስተር ፕላን መዘጋጀቱን ጠቁመዋል። ለረቂቅ ማስተር ፕላኑ የሚሆን ጥናት በማዘጋጀት ረገድ የተለያዩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተውጣጡ ምሁራን መሳተፋቸውንም ተናግረዋል፡፡ ረቂቅ ማስተር ፕላኑ ከመዲናዋ የሚመነጨውን ደረቅ ቆሻሻ ህብረተሰቡን ባሳተፈና በተደራጀ መልኩ ሰብስቦ በማስወገድ ከተማዋን ውብ፣ፅዱና ምቹ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑንም ጠቁመዋል። ይህም ደረቅ ቆሻሻን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋል ሚናው የጎላ ስለመሆኑም ነው የተናገሩት፡፡ በጥናቱ የተሳተፉት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኬሚካልና ባዮ ምህንድስና ትምህርት ክፍል መምህር ሽመልስ ከበደ (ዶ/ር) ጥናቱን ባቀረቡበት ወቅት፤ በከተማዋ በቀን በአማካኝ 2 ሺህ 900 ቶን ደረቅ ቆሻሻ እንደሚመነጭ ተናግረዋል፡፡ ከዚህም ውስጥ 70 በመቶ የሚሆነው በአግባቡ በመሰብስብና በማደራጀት እንደሚወገድ በጥናቱ መመላከቱን ጠቅሰው፤ 12 በመቶ የሚሆነው ደግሞ ለተፈጥሮ ማዳበሪያና የሃብት ምንጭ መፍጠሪያ እንደሚውል ተናግረዋል፡፡ ቀሪው በተገቢው መንገድ እየተወገደ አለመሆኑም ተገልጿል። ይህም ህዝብን ባሳተፈ መልኩ የቆሻሻ አወጋገድ ሰርዓትን በማዘመን መልሶ ጥቅም ላይ ማዋል እንደሚገባ ያመላክታል ነው ያሉት፡፡ ከዚህ አኳያ የተቀናጀ የደረቅ ቆሻሻ አስተዳደር ረቂቅ ማስተር ፕላኑ በከተማዋ ዘመናዊ የቆሻሻ አወጋገድ ስርዓት እንዲኖር ሚናው የጎላ ነው ብለዋል፡፡        
በዓድዋ ድል መታሰቢያ በቅርቡ አገልግሎት የጀመረው የብዙኃን ትራንስፖርት ተርሚናል ምቹ እና እንግልትን እንደሚቀንስ ተጠቃሚዎች ገለጹ
Apr 22, 2024 115
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 14/2016 (ኢዜአ)፦ በዓድዋ ድል መታሰቢያ በቅርቡ አገልግሎት የጀመረው የብዙኃን ትራንስፖርት ተርሚናል ለተጠቃሚዎች ምቹና ደህንነቱ የተጠበቀ እንዲሁም እንግልትን የሚያስቀር መሆኑን ተጠቃሚዎች ገለጹ። በመዲናዋ ምቹ የብዙኃን ትራንስፖርት ማስተናገጃ ጣቢያዎች በብዛት አለመኖራቸው የትራንስፖርት ተጠቃሚዎችን ለተለያየ እንግልት ሲዳርጉ ይስተዋላል። የትራንስፖርት ማስተናገጃዎች በብዛት መጠለያ የሌላቸው በመሆናቸው ተጠቃሚዎች ለዝናብና ፀሐይ ይጋለጣሉ፤ መሳፈሪያ ጣቢያዎቹ ብዙ ህዝብ የሚንቀሳቀስባቸው በመሆናቸው ለሌብነት ይዳረጋሉ። በመሃል ፒያሳ በዓድዋ ድል መታሰቢያ የተገነባው የብዙኃን ትራንስፖርት ማስተናገጃ አገልግሎት በቅርቡ የተርሚናል አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ይታወሳል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የትራንስፖርት ተጠቃሚዎች እንዳሉት፤ በዓድዋ ድል መታሰቢያ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የብዙሃን ትራንስፖርት ተርሚናል ምቹ እና በፊት የነበሩ እንግልቶችን የሚቀንስ ነው። አቶ መስፍን ቶሎሳ እና አቶ ይስሐቅ ሳህሌ ከዚህ ቀደም በአካባቢው አውቶብስ ለመሳፈር ብዙ እንግልት እንደነበርና ለሌቦችም ይጋለጡ እንደነበር አውስተው፥ በዓድዋ ድል መታሰቢያ የተገነባው ማስተናገጃ ሌብነትን ያስቀረ እና ለተገልጋዮች ምቹ የሆነ ነው ብለዋል። ተርሚናሉ በቂ መጠለያ ያለው በመሆኑ ህብረተሰቡ አውቶብስ በሚጠብቅበት ወቅት ሊያጋጥመው ከሚችል ዝናብና ፀሐይ መገላገሉንም አንስተዋል። ወይዘሮ ሂሩት ኪሮስ በበኩላቸው፥ ተርሚናሉ ዘመናዊና በቂ መቀመጫዎች ያሉት በመሆኑ ተጠቃሚዎች አውቶብስ እስኪመጣ በተረጋጋ ሁኔታ የሚጠብቁበት እድል መፈጠሩንም ጠቅሰዋል።   የዓድዋ ድል መታሰቢያ ዋና ዳይሬክተር ኢንጅነር ውባየሁ ማሞ በበኩላቸው፤ በቅርቡ አገልግሎት መስጠት የጀመረው የብዙኃን ትራንስፖርት ተርሚናል ለበርካታ ሰዎች አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከዚህ በፊት በአብዛኛው የፒያሳ አካባቢ የትራፊክ መጨናነቅ ብሎም ተጠቃሚዎች ለዝናብና ፀሐይ ሲጋለጡ እንደነበርም አውስተዋል። አሁን ላይ የዓድዋ ድል መታሰቢያ የብዙሃን ትራንስፖርት ማስተናገጃ አገልገሎት መጀመሩ የነበሩ ችግሮችን ያስቀራል ብለዋል። ተርሚናሉ ለአዛውንትና አካል ጉዳተኞችም ምቹ የሆነ፣ በቂ የደህንነት ማስጠበቂያ ካሜራዎች የተገጠሙለት መሆኑን ጠቅሰው፥ ከመንገድ ውጭ በመሆኑም የትራፊክ መጨናነቅን እንደሚቀንስ ተናግረዋል። ከትራንስፖርት ቢሮ ጋር በመሆን ተርሚናሉ በዘላቂነት ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲሰጥ እየተሰራ ነው ብለዋል።      
ባለፉት ዘጠኝ ወራት በመዲናዋ ከእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች 11 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር የሚገመት ንብረት ማዳን ተችሏል- ኮሚሽኑ
Apr 22, 2024 115
አዲስ አበባ ፤ ሚያዚያ 14/2016 (ኢዜአ)፦ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በመዲናዋ ለተከሰቱ የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች ፈጣን ምላሽ በመስጠት 11 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር የሚገመት ንብረት ከውድመት ማዳን መቻሉን የአዲስ አበባ እሳትና አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን አስታወቀ፡፡ የኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ባለሙያ ንጋቱ ማሞ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የእሳት ቃጠሎ፣ በግንባታ ወቅት የሚከሰት አደጋ፣ የመሬት መንሸራተትና ጎርፍ በመዲናዋ ተደጋግመው ከሚከሰቱ አደጋዎች መካከል ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በመዲናዋ እና አካባቢዋ 392 አደጋዎች አጋጥመዉ 670 ሚሊየን ብር የሚገመት ንብረት መውደሙን ተናግረዋል፡፡ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች ባደረጉት ፈጣን የአደጋ መቆጣጠር ርብርብ 11 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር የሚገመት ንብረት ማዳን ተችሏል ብለዋል። የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች 39 ሰዎችን ከእሳት አደጋ፤ 85 ሰዎችን ደግሞ ከሌሎች ድንገተኛ አደጋዎች በድምሩ 124 ሰዎችን በህይወት ማትረፍ እንደቻሉም ጠቁመዋል። በሌላ በኩል በኮንስትራክሽን ፣ ተቆፍረው ክፍት በተቀመጡ ጉድጓዶች ምክንያት ህይወታቸው ያለፉ ሰዎች መኖራቸውን ተናግረዋል። በዘጠኝ ወራት የደረሱ አደጋዎች ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር የንብረት ውድመት መጠን በ37 ሚሊየን ብር መቀነሱን ጠቅሰዋል። ህብረተሰቡ የእሳትና ድንገተኛ አደጋዎችን የመከላከልና መቆጣጠር ስራን የበለጠ እንዲያግዝም ጥሪ አቅርበዋል።
የኢትዮጵያ ተስማሚነት ምዘና ድርጅት ባለፉት 9 ወራት የአፈር ማዳበሪያን ጨምሮ ከ19 ሺህ በላይ የምርት ጥራት ፍተሻ አገልግሎቶች ሰጠ
Apr 22, 2024 191
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2016 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ተስማሚነት ምዘና ድርጅት ባለፉት 9 ወራት የአፈር ማዳበሪያን ጨምሮ ከ19 ሺህ በላይ የምርት ጥራት ፍተሻ አገልግሎት መስጠቱን አስታወቀ። ድርጅቱ ዋና ዳይሬክተር መዓዛ አበራ ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ድርጅቱ በዋናነት የጥራት ፍተሻ ላቦራቶሪ፣ የጥራት ሰርተፊኬሽን እና የኢንስፔክሽን አገልግሎቶችን እየሰጠ ይገኛል። በዚህም ባለፉት 9 ወራት ከአንድ ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን በላይ የአፈር ማዳበሪያን ጨምሮ ከ19 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ምርቶች በላብራቶሪ የጥራት ፍተሻና የሰርተፊኬሽን አገልግሎት መስጠቱን ገልጸዋል፡፡ ጅቡቲ በሚገኘው የድርጅቱ ቅርንጫፍም ከ31 ሚሊዮን ሊትር በላይ የምግብ ዘይት ላይ የላቦራቶሪ ፍተሻ ማድረጉን ነው ያነሱት። ድርጅቱ የጥራት ፍተሻ አገልግሎት ከሚሰጣቸው ዘርፎች መካከል የግብርና ግብዓቶች፣ የምግብና መጠጥ፣ መድሃኒት፣ ኬሚካልና ማዕድን፣ የኮንስትራክሽን ግብዓት፣ የኤሌክትሮኒክስ የቆዳና ጨርቃጨርቅ ምርቶች ይገኙበታል። ምርቶቹ በተቀመጠላቸው መስፈርት መሰረት ደረጃቸውን ጠብቀው መመረታቸው ተፈትሾ የማረጋገጫ ሰርተፊኬት የተሰጣቸው መሆኑንም ነው የተናገሩት። ድርጅቱ የሚሰጣቸው አገልግሎቶች ዓለም አቀፍ ዕውቅናና ተቀባይነት ያላቸው መሆኑንም ዋና ዳይሬክተሯ አንስተዋል። የፍተሻ ላቦራቶሪዎቹ ዘመናዊና ጥራታቸውን የጠበቁና በዓለም አቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያላቸው በመሆናቸው የህብረተሰቡን ደህንነትና ጤንነት ለማስጠበቅ ወሳኝ ሚና አላቸው ብለዋል። በመንግስት ከውጭ የሚገቡና በአገር ውስጥ የሚመረቱ ምርቶች የተቀመጠላቸውን የጥራት መስፈርት ማሟላታቸውን ማረጋገጥ ላይ ልዩ ትኩረት መደረጉንም ተናግረዋል። ድርጅቱ የጥራት ፍተሻና የማረጋገጫ ሰርተፊኬት ከሰጠ በኋላም በምርቶቹ ላይ በየሶስት ወሩ ፍተሻ እንደሚያደርግ ነው ያነሱት። ፍተሻ ተደርጎባቸው ከሁለት ጊዜ በላይ የተቀመጠላቸውን የጥራት መስፈርት ያላሟሉ ምርቶችን ለሚመለከተው ተቆጣጣሪ አካል በማሳወቅ በምርቶቹ ላይ ክትትልና ቁጥጥር እንዲያደርግ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ ተስማሚነት ምዘና ድርጅት በየክልሉ 9 ቅርንጫፎች ያሉት ሲሆን ህብረተሰቡ አስገዳጅ የጥራት ምልክቶችና የምርት ደረጃዎች ላይ ያለውን ግንዛቤ ለማሳደግ ከባለደርሻ አካላት ጋር እየሰራ ነው ብለዋል።  
በብሄራዊ ፓርኩ የተነሳውን የእሳት ቃጠሎ ለመቆጣጠር በተደረገ ርብርብ   እንዳይዛመት መከላከል ተቻለ
Apr 22, 2024 94
ጎንደር ፤ሚያዚያ 14 /2016(ኢዜአ)፡- በሰሜን ተራሮች ብሄራዊ ፓርክ የተነሳውን የእሳት ቃጠሎ ለመቆጣጠር በተደረገ ርብርብ እሳቱ እንዳይዛመት መከላከል መቻሉን የፓርኩ ጽህፈት ቤት አስታወቀ፡፡ በጽህፈት ቤቱ የአግሮ ኢኮሎጂና የዱር እንስሳት ተመራማሪ አቶ ታደሰ ይግዛው ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ የእሳት ቃጠሎው የተነሳው በፓርኩ ክልል አምባራስ በተባለው ቀበሌ ውስጥ ነው፡፡ የእሳት ቃጠሎው የተነሳው ሚያዚያ 10 ቀን 2016 ዓ.ም ጠቅሰው፤ ቃጠሎው በተነሳበት አካባቢ በጓሳ ሳርና ውጨና በተባሉ የፓርኩ የተፈጥሮ የደን ዛፎች ላይ ጉዳት ማድረሱን አመልክተዋል፡፡ በፓርኩ የዱር እንስሳት ላይ እስካሁን ቃጠሎው ያደረሰው ጉዳት እንደሌለ ጠቁመው፤ የቃጠሎው ምክንያት በውል አለመታወቁንም ተናግረዋል። በፓርኩ የእሳት አደጋ ተከላካይ ብርጌድ አባላት፣ በነዋሪዎችና በአጋር አካላት ተሳትፎ በተደረገው የመከላከል ስራ ግጭና እሜት ጎጎ በተባሉ ጎጦች ቃጠሎውን በመቆጣጠር ወደ ፓርኩ የተለያዩ አካባቢዎች እንዳይዛመት መከላከል መቻሉን አስታውቀዋል፡፡   ሙሉ በመሉ ለመቆጣጠርም ርብርቡ ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። የአካባቢው ሞቃታማና ነፋሻማ የአየር ሁኔታ ለቃጠሎው መባባስ ምክንያት መሆኑን ገልጸው፤ እሳቱ ያደረሰውን የጉዳት መጠን በዝርዝር ለማወቅ በቀጣይ ቀናት በሚቋቋም ግብረ ሃይል ጥናት ይደረጋል ብለዋል፡፡ በፓርኩ ክልል ባለፉት ዓመታት በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ ችግር ተደጋጋሚ የእሳት ቃጠሎ ተከስቶ እንደነበር አስታውሰው፤ ሆኖም የከፋ ጉዳት ሳያደርስ መቆጣጠር ተችሎ እንደነበር አመልክተዋል፡፡ በቃጠሎው ጉዳት የደረሰበትን የፓርኩን የተፈጥሮ ሀብት መልሶ እንዲያገግም በማድረግ በኩልም በየዓመቱ ክረምት ሀገር በቀል ችግኞች በመትከል የክብካቤ ስራ ሲከናወን መቆየቱንም አስረድተዋል፡፡ 412 ስኩየር ኪሎ ሜትር ስፋት ያለው ፓርኩ ውስጥ ዋልያ፣ ቀይ ቀበሮና ጭላዳ ዝንጀሮን ጨምሮ የብርቅዬ የዱር እንስሳትና አእዋፋት መገኛ መሆኑ ይታወቃል፡፡    
በአፍሪካ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብርና ስርዓትን ማጠናከር ይገባል--በለጠ ሞላ( ዶ/ር)
Apr 22, 2024 115
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 14/2016 (ኢዜአ)፦በአፍሪካ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብርና ስርዓትን ማጠናከር እንደሚገባ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ ( ዶ/ር) ገለጸ። ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ የታገዘ ዘመናዊ ግብርናን በማስፋት በምግብ ራስን ለመቻል በቁርጠኝነት እየሰራች መሆኗንም ተናግረዋል። ሚኒስትሩ ይህን ያሉት በአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን ለሁለት ቀናት እየተካሄደ በሚገኘው ስድስተኛው የአፍሪካ የሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ጉባኤ መክፈቻ መርሐ ግብር ላይ ነው። ጉባኤው “የ2030 የዘላቂ ልማት አጀንዳን ለማሳካት እና በ2063 በአፍሪካ ድህነትን ለማጥፋት የቴክኖሎጂና የፈጠራ መፍትሔዎችን በአግባቡ መተግበር” በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ይገኛል። የኢኖቬሽንና ቴከኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) አፍሪካ ተስፋ ሰጪ ጉዞ ላይ ብትሆንም ያልተሻገረቻቸው ችግሮች መኖራቸውን ገልጸዋል። ድህነት፣ የሰላምና ፀጥታ ችግርና የልማት አለመረጋገጥ ከፈተናዎች መካከል ናቸው ያሉት ሚኒስትሩ፥ ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ፈጠራ አፍሪካን ካለችበት ችግር ለማውጣት ወሳኝ መሳሪያዎች ናቸው ብለዋል። በግብርና፣ በታዳሽ ሃይል እና በጤናው ዘርፍ የቴክኖሎጂ ፈጠራዎችን በመተግበር የህዝቡን ኑሮ ማሻሻል፣ ስራ ፈጠራን ማስፋት እና ድህነትን መቀነስ እንደሚገባ ጠቁመዋል። በአህጉሪቱ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የፈጠራና የቴክኖሎጂ ስራዎችን ለመተግበርም ተቋማት በባህል ለውጥና በፖሊሲ አተገባበር ላይ ጉልህ ድርሻ እንዳላቸው ተናግረዋል። የመንግስት ተቋማት፣ የግል ዘርፍ፣ የምርምር ተቋማት፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች እና ዓለም አቀፍ የልማት አጋሮች የእውቀት፣ የሀብትና የሙያ ትብብር ወሳኝ እንደሆነ ጠቁመዋል። ሚኒስትሩ አክለውም ኢትዮጵያ የግብርና ዘርፉን ለማዘመን እና የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራች መሆኗን ገልጸዋል። ለዚህም የስርዓተ ምግብ ሽግግር ፍኖተ ካርታ በማዘጋጀት ምርታማነትን ለማሳደግና ከተረጂነት ለመላቀቅ ቴክኖሎጂ መር ልማት እየተተገበረ ነው ብለዋል። ከዚህም ባሻገር የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂን በመቅረፅ በሀገሪቱ መሰረታዊ የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ትግበራ እየተከናወነ መሆኑንም አውስተዋል።   በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚ ኮሚሽን ምክትል ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ፔድሮ በበኩላቸው፥ አፍሪካ እንድታድግ የሰው ሀይል ልማት፣ ምርምር እና የቴክኖሎጂ ሽግግር እና ሰው ሰራሽ አስተውሎት ላይ በትኩረት መስራት አለባት ብለዋል። አህጉሪቱ በሰብል ምርት፣ በእንስሳትና በአሳ ሀብት ያልተነካ እምቅ አቅም እንዳላት ጠቅሰው፥ ይህን ወደ ጥቅም ለመቀየርና የሚሊዮኖችን ህይወት ለማሻሻል በቴክኖሎጂ የታገዘ ዘመናዊ ግብርና ወሳኝ እንደሆነ ተናግረዋል።  
የሜካናይዝድ ሃይል የኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ጸንቶ እንዲቆይ የተጫወተውን የላቀ ሚና ለማስቀጠል ዘመኑን በሚዋጅ ብቃት የማጠናከር ስራ ይከናወናል − ሌተናል ጄኔራል ይመር መኮንን
Apr 21, 2024 173
አዋሽ አርባ፤ ሚያዝያ 13/2016(ኢዜአ)፡- የሜካናይዝድ ሃይል የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ተጠብቆና ፀንቶ እንዲቆይ የተጫወተውን የላቀ ሚና ለማስቀጠል ዘመኑን በሚዋጅ ብቃትና ጥራት የማነጽ ተግባር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን በሀገር መከላከያ ሰራዊት የትምህርትና ስልጠና መምሪያ ዋና አዛዥ ሌተናል ጄኔራል ይመር መኮንን ገለጹ። በሀገር መከላከያ ሰራዊት የሜካናይዝድ ዕዝ የአዋሽ አርባ ውጊያ ቴክኒክ ትምህርት ቤት 46ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ከፍተኛ ጄኔራል መኮንኖች በተገኙበት ዛሬ በተለያዩ ዝግጅቶች ተከብሯል። በዚህ ወቅት በሀገር መከላከያ ሰራዊት የትምህርትና ስልጠና ዋና መምሪያ ዋና አዛዥና የዕለቱ የክብር እንግዳ ሌተናል ጄኔራል ይመር መኮንን እንደገለጹት፤ ትምህርት ቤቱ ያፈራቸው የሜካናይዝድና ሞተረኛ የሰው ሃይል የኢትዮጵያ ሉዓላዊነትን በማፅናት ረገድ ወሳኝ የላቀ ሚና ተጫውቷል።   ይህን የላቀ ሚናውን ለማስቀጠል የሜካናይዝድ የስልጠናና ስርዓተ ትምህርት በመከለስና በአዲስ መልክ በማዘጋጀት ዘመኑን የዋጀ የውጊያ ቴክኒክ ስልጠናና የዘርፉ የሰው ሃይል ልማት እየተከናወነ መሆኑን አመልክተዋል። በተለይም የመከላከያ ፍላጎትን ያገናዘበ በሜካናይዝድ ቴክኖሎጂ ዕውቀት፣ ክህሎትና አጠቃቀም የበቁ ምድብተኞች፣ አመራሮችና አሽከርካሪዎች ለማፍራት በትኩረት እንደሚሰራም ጠቅሰዋል። በተለይ ትምህርት ቤቱ የሜካናይዝድ የትምህርትና ስልጠና የልህቀት ተቋም ለማድረግ በዘርፉ የተጀመሩ ሪፎርም ስራዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመው፤ ትምህርት ቤቱን በዘመናዊ የሜካናይዝድና ሞተራይዝድ ቴክኖሎጂ በማደራጀት ስልጠና እንዲሰጥ መደረጉን ገልጿል።   ዘመናዊ ትጥቆችን በአግባቡ መጠቀም እንዲችል በስልጠናና በዲስፕሊን የታነፀ ዘመኑን የሚዋጅ ብቃት ያላቸውን ሜካናይዝድ ሙያተኞችን በጥራትና በብዛት ለማፍራት እየሰራን ነው ሲሉ አስታውቀዋል። የአዋሽ አርባ ውጊያ ቴክኒክ ትምህርት ቤት 46ኛውን የምስረታ በዓል ትምህርት ቤትን አሁን ካለበት ደረጃ ወደ ላቀ ምዕራፍ ለመውሰድ የመከላከያ ተቋምን ዕቅድና ፍላጎት በዘላቂነት ለማሳካት ቃል የሚገባበት መሆኑን አስረድተዋል።   በሀገር መከላከያ ሰራዊት የሜካናይዝድ ዕዝ ዋና አዛዥ ሜጄር ጄኔራል ከፍያለው አምዴ በበኩላቸው፤ ትምህርት ቤቱን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሳደግ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በሁሉም የሜካናይዝድ ቴክኖሎጂ የበቁና የግዳጅ ተልዕኮውን በከፍተኛ ደረጃ መፈጸም የሚችል ሃይል የመገንባት ስራው ተጠናክሮ ይቀጥላል ነው ያሉት። በተለይ ከወቅቱ ተለዋዋጭ ሁኔታዎች ጋር መራመድ የሚችል የሜካናይዝድና ሞተራይዝ ሃይል ግንባታና የዘመኑ የስልጠና ቴክኖሎጂን አጠቃቀም ላይ የመከላከያ ሃይሉን አቅም ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ ትኩረት መሰጠቱን አስረድተዋል።   ትምህርት ቤቱ በ1970 ዓ.ም ሲመሰረት በወቅቱ በምስራቁ ክፍል የነበረውን ወረራ ለመመልከት ነበር ያሉት ደግሞ የአዋሽ አርባ የውጊያ ቴክኒክ ትምህርት ቤት አዛዥ ኮሎኔል ባለው ምንተስኖት ናቸው። ትምህርት ቤቱ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ የታንከኛ፣ መድፈኛና ሞተራይዝድ ክፍሎች በማብቃት በየዘመኑ የተቃጡ ወረራዎችን በማክሸፍ ሚናውን መወጣቱን ተናግረዋል። ሰፊ ክህሎትና ልምድ ያለበት ከመሆኑም ባለፈ የስነ ልቦናና አዲስ የስልጠና መመሪያዎችን በማዘጋጀት የተሻለ የመካናይዝድ አቅም ለመፍጠር አሁንም በሙሉ አቅማችን እንሰራለን ሲሉ ገልጸዋል። በክብረ በዓሉ ላይ የባለፉት 46 ዓመታት የውጊያ ቴክኒክ ትምህርት ቤት የዕድገት ጉዞና አሁን ያለበት ደረጃን የሚያሳይ የፎቶና መካናይዝድ አውደ ርዕይ በእንግዶች ተጎብኝተዋል።
በጋምቤላ የወባ ወረርሽኝ ለመከላከል የሚያስችሉ ተግባራት በመከናወን ላይ ናቸው
Apr 21, 2024 82
ጋምቤላ፤ ሚያዝያ 13/2016(ኢዜአ)- በጋምቤላ ክልል መጪውን የክረምት መግቢያ ተከትሎ የወባ ወረርሽኝ እንዳይከሰት አስፈላጊው የቅድመ መከላከል ዝግጅት ስራ እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ጤና ቢሮ አስታወቀ። በቢሮው የወባ መከላከል ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ አዲሱ ጦና ለኢዜአ እንደገለጹት ሁሉም የክልሉ ወረዳዎች የወባ ተጋላጭ በመሆናቸው የቅድመ መከላከልና ጥንቃቄ ስራዎች ከወዲሁ እየተከናወኑ ናቸው። በተለይም ባለፉት ሁለት ዓመታት በክልሉ የክረምቱን መግቢያና መውጫ ተከትሎ ከቀዳሚዎቹ ዓመታት በተለየ በሽታው ጨምሮ እንደነበር አስታውሰዋል። በመሆኑም ባለፉት ሁለት ዓመታት በክረምቱ መግቢያና መውጫ የነበረው ዓይነት የወባ በሽታ ዳግም እንዳይከሰት የቅድመ ጥንቃቄ ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን ተናግረዋል። የወባ ትንኝ መከላከያ አጎበር ማሰራጨት፣ የፀረ- ወባ ኬሚካል ርጭት ማካሄድ፣ የአካባቢ ጽዳትና ቁጥጥር ስራዎች ማጠናከርና የህብረተሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ ደግሞ በሽታውን ለመከላከል እየተሰሩ ከሚገኙ የመከላከል ተግባራት መሆናቸውን ገልጸዋል። በበሽታው የተያዙ ሰዎች በአቅራቢያቸው በሚገኙ የጤና ተቋማት የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ አስፈላጊው የህክምና ግብዓት ወደ ጤና ተቋማት እንዲደርስ እየተደረገ መሆኑንም አክለዋል። ጋምቤላ ከተማን ጨምሮ በአራት ከፍተኛ የወባ ተጋላጭ ወረዳዎች የአጎበር ስርጭት እንደሚካሄድ ጠቁመው በዲማና በጎደሬ ወረዳ ከሚያዝያ 14 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ 50 ሺህ አጎበሮች ለማሰራጨት ታቅዷል ብለዋል። እንዲሁም በክልሉ አስር ወረዳዎችና ስድስት የስደተኛ መጠለያ ጣቢያዎች ከ148 ሺህ በሚበልጡ ቤቶች ላይ የፀረ- ወባ ኬሚካል ርጭት ለማካሄድ የቅድመ ዝግጀት ስራዎች መጠናቀቃቸውን አስረድተዋል። ከተጠቀሱት ስራዎች ጎን ለጎንም በክልሉ ሁሉም ወረዳዎች አጎበርን በአግባቡ በመጠቀም፣ አካባቢን በማጽዳት ወባን መከላከል እንደሚቻል ማህበረሰቡን ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራዎች እየተከናወኑ እንደሚገኝም አቶ አዲሱ ገልጸዋል። የጋምቤላ ከተማ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል ስራ አስኪያጅ አቶ ሮን ጉኝ እንዳሉት በበጋው ወራትም በወባ በሽታ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር ቢኖሩም በክረምቱ መግቢያና መውጫ ወቅት በበሽታ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በእጅጉ ይጨምራል ብለዋል። ሆስፒታሉ ይህንን ታሳቢ በማድረግ የክረምቱን መግቢያ ተከትሎ ለሚጨምረው የወባ በሽታ አስፈላጊው የህክምና ግብዓት መቅረቡን ጠቁመው ወደ ህክምና ለሚመጡት ታካሚዎች ስለ በሽታው ያላቸውን ግንዛቤ ለማሳደግ ትምህርት እየተሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል። የወባ በሽታ በበጋ ወራት የሚቀንስ ቢሆንም በክረምት ወራት በጅጉ እንደሚጨምር የገለጹት ደግሞ በሆስፒታሉ ሲታከሙ ያገኘናቸው የጋምቤላ ከተማ ነዋሪ አቶ ጋድቤል ቤል ናቸው። በመሆኑም በክረምቱ ወራት አካባቢያቸውን በማጽዳትና የወባ ትንኝ መከላከያ አጎበር በአግባቡ በመጠቀም ከበሽታው እራሳቸውን ለመጠበቅ ጥረት እንደሚያደርጉ ነው ታካሚው የገለጹት።      
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም