ፖለቲካ
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሳታፊና ጤናማ ፉክክር የሚታይበት የፖለቲካ አውድ እየተፈጠረ ነው
Mar 27, 2025 21
አሶሳ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ):- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ሰፊ የፖለቲካ ምህዳር በመፈጠሩ አሳታፊና ጤናማ ፉክክር የሚታይበት የፖለቲካ አውድ እየተፈጠረ መሆኑን የክልሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ገለጸ። የምክርቤቱ ሰብሳቢና የቤኒሻንጉል ህዝቦች ነፃነት ንቅናቄ (ቤህነን) ፓርቲ ሊቀመንበር አብዱሰላም ሸንገል፤ ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ በተለይም በክልሉ ያለውን የፖለቲካ እንቅስቃሴ በተመለከተ ከኢዜአ ጋር ቆይታ አድርገዋል። በክልሉ 10 የፖለቲካ ፓርቲዎች በሰላማዊ መንገድ እየተንቀሳቀሱ መሆኑን የጠቀሱት አብዱሰላም፤ የዚህ ተሳትፎ መሰረቱ የፖለቲካ ምህዳሩ እየሰፋና በሃሳብ የበላይነት በክርክር የሚያምን ትውልድ እየተፈጠረ በመምጣቱ መሆኑን ተናግረዋል። ከለውጡ በፊት የተፎካካሪ ፓርቲ አደረጃጀቱን ለማስፋት ከባድ ፈተና እንደነበር አስታውሰው አሁን ግን የፖለቲካ ምህዳሩ እየሰፋ የፖለቲካ ፓርቲ የመደራጀትና አባላትን ማፍራት የሚችልበት ምቹ ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል። በክልሉ ሰፊ የፖለቲካ ምህዳር በመፈጠሩ አሳታፊና ፉክክር የሚታይበት የፖለቲካ አውድ እየተፈጠረ ይገኛልም ነው ያሉት። ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከገዢው ፓርቲ ጋር በክልልና በሀገር አቀፍ ደረጃ በሀሳብ እየተከራከሩ አብሮ የመስራት ልምድ እየዳበረ ስለመሆኑም አንስተዋል። የፖለቲካ ፓርቲዎች ዋነኛ ዓላማ የህዝብን አንድነት ማጠናከር፣ የሀገሪቱን ሰላምና ልማትን ማስቀጠል መሆኑን ጠቅሰው በሀገር ብሄራዊ ጥቅምና ሉአላዊነት ላይ ልዩነት ሊኖር አይገባም ብለዋል። በክልሉ የመንግስት ኃላፊነት ላይ የተፎካካሪ ፓርቲ አመራሮች ስልጣን ይዘው እየሰሩ መሆኑንና ለአብነትም እሳቸው የካቢኔ አባል እንደሆኑ ገልጸዋል። የክልሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክርቤት ከክልሉ መንግስት ጋር ውይይት ለማድረግ በሚፈልግበት ጊዜ ምቹ ሁኔታዎች መኖራቸውን እና የሚያጋጥሙ ችግሮችን በንግግር እየፈቱ መሆኑንም ተናግረዋል። የተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች በሃሳብ እና ሰላማዊ መንገድን ተጠቅመው ለሀገሪቱ ሁለንተናዊ ዕድገት እያደረጉት ያለውን ተሳትፎ አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጠይቀዋል።
ኢትዮጵያ ህገወጥ የጦር መሳሪያ ዝውውርን ለመቆጣጠር በቁርጠኝነት እየሰራች ነው-አምባሳደር ባጫ ደበሌ
Mar 27, 2025 17
አዲስ አበባ፤መጋቢት 18/2017 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በቀጣናው እና በአፍሪካ ህገወጥ የቀላል መሳሪያ ዝውውር ለመከላከል እና ለመቆጣጠር በቁርጠኝነት እየሰራች እንደምትገኝ በኬንያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ባጫ ደበሌ ገለጹ። አምባሳደር ባጫ ደበሌ ከቀጣናዊ የቀላል የጦር መሳሪያ ቁጥጥር ማዕከል ዋና ፀሐፊ ጂን ፒዬር ቤቲንዲጅ ጋር ዛሬ በናይሮቢ ተወያይተዋል። ውይይቱ ማዕከሉ በቀጣናው ህገ ወጥ የቀላል የጦር መሳሪያዎች እና አነስተኛ ትጥቆች ዝውውር የመቆጣጠር አቅሙን ማሳደግ በሚችልበት ሁኔታ ላይ ያተኮረ ነው። አምባሳደር ባጫ ኢትዮጵያ በቀጣናው ዘላቂ ሰላም እና መረጋጋት እንዲሰፍን ቁርጠኝነት እንዳላት ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ህገወጥ የአነስተኛ ጦር መሳሪያ ዝውውርን ለመቆጣጠር እየተደረገ ባለው ጥረት ያላትን ሚና አጠናክራ እንደምትቀጥል አመልክተዋል። የቀጣናዊ የቀላል የጦር መሳሪያ ቁጥጥር ማዕከል (RECSA) ዋና ፀሐፊ ጂን ፒዬር ቤቲንዲጅ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ሰላም እና መረጋጋት እንዲሰፍን በሀገራት መካከል ያለውን ትብብር ለማሳደግ ያላትን ቁርጠኝነት አድንቀዋል። ኢትዮጵያ በቀጣናው እና አፍሪካ ህገ ወጥ የቀላል የጦር መሳሪያዎች ዝውውር በመቆጣጠር ጥረቶች ውስጥ ቁልፍ አጋር መሆኗን በናይሮቢ የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመለክታል። ኢትዮጵያ የህገወጥ መሳሪያ ዝውውር ቁጥጥር ማድረግ ለደህንነት እና ዘላቂ ልማት መረጋጋጥ ከፍተኛ ሚና እንዳለው በጽኑ እንደምታምንም ተገልጿል።
በክልሉ ለሰላምና ፀጥታ ዘርፍ ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት በተሰሩ ስራዎች አንጻራዊ ሰላም ማስፈን ተችሏል - ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Mar 27, 2025 69
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 18/2017(ኢዜአ)፦ በክልሉ ለሰላምና ፀጥታ ዘርፍ ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት በተሰሩ ስራዎች አንጻራዊ ሰላም ማስፈን ተችሏል ሲሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለጹ። ርዕሰ መስተዳድሩ ከክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አመራሮች ጋር በሰላምና ፀጥታ ዙሪያ በወላይታ ሶዶ ከተማ ያደረጉት ምክክር ቀጣይ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ ተጠናቋል።   ርዕሰ መስተዳድሩ በመድረኩ ማጠቃለያ እንደገለፁት፤ ኢ-ተገማች በሆነው የአለም ሁኔታ ክልላዊ፤ ሀገራዊና አለም አቀፋዊ ነባራዊ ሁኔታን ፈጥኖ በመረዳት ሁሌም ቀድሞ ለመገኘት ዝግጁ መሆን ያስፈልጋል ብለዋል። የክልሉ መንግስት ለሰላምና ፀጥታው ዘርፍ ቅድሚያ ትኩረት በመስጠት ባከናወናቸው ዘርፈ ብዙ ስራዎች በክልሉ አንጻራዊ ሰላም ማስፈን መቻሉን ጠቅሰው፤ ይህም ክልሉ ከልማት ስራዎች ባሻገር ትልልቅ ሀገራዊ ኩነቶችን በስኬት ማስተናገድ ማስቻሉን ገልጸዋል፡፡ ሰላም የሁሉም ነገር መሠረት ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ በክልሉ በሰላም በኩል የተመዘገበው ስኬት የኢንቨስትመንት ፍሰትና የቱሪዝም ዘርፍን በከፍተኛ ሁኔታ በማነቃቃት ለፈጣን ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና ለዘላቂ ልማት ምቹ መደላድል መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም በክልሉ በሰላምና ፀጥታ ዘርፍ ለተመዘገበው አመርቂ ውጤት ህብረተሰቡ እና የፀጥታ ሀይሉ ሊመሰገኑ ይገባል ማለታቸውን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጽህፈት ቤት መረጃ ያመላክታል። ሰላም በጊዜና በቦታ ሳይገደብ ሁሌም የሁሉም ነገር ቀዳሚ ተግባር መሆኑን ጠቁመው፤ የፖሊስ መኮንኖች ነፃና ገለልተኛ ሆነው፤ ሞያዊ ስነምግባሩን በተግባር በመላበስና ኃላፊነታቸውን በአግባቡ በመወጣት ህብረተሰቡን በቅንነት ማገልገል ይጠበቅባቸዋል ነው ያሉት፡፡ በቀጣይም ጊዜያዊና ወቅታዊ ፈተናዎችን በብቃት መሻገር የሚችል የፖሊስ ሰራዊት እና ጠንካራ ተቋም ለመገንባት የተጀመሩ ስራዎች ተጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባም ተናግረዋል። ከነባራዊ ሁኔታዎች አኳያ ዕቅዶችን መከለስ፤ በጠንካራ ተቋማዊ አሰራር መምራትና መፈፀም፤ ሞያዊ ስነምግባርን ጠብቆ ለሕግና ለሕገመንግስታዊ ስርዓቱ ታማኝ በመሆንና ከህብረተሰቡ ጋር ይበልጥ ተቀራርቦ በመስራት የተጀመሩ የሰላም ግንባታ ተግባራትን ከግብ ማድረስ ይገባል ነው ያሉት። የሽግግር ፍትህ ስራዎች ትግበራን መከታተልና የጠንካራ ተቋም ግንባታ ስራዎችን በማጠናከር የዘርፉን ውጤታማነት ለማሳደግ መስራት እንደሚገባም ገልጸዋል። የዲጂታል ዘመኑን በዋጀ አግባብ የሰላምና ፀጥታውን ዘርፍ የመረጃ ስርዓት ማዘመንና በነባራዊ ሁኔታዎች ግምገማና ሳይንሳዊ የመረጃ ትንተናን መሠረት ባደረገ መልኩ ህግ የማስከበር ዝግጁነትን ማሳደግ ይገባል ብለዋል። የሚዲያ አውታሮችን በህዝቦች መካከል ጥርጣሬን፤ ጥላቻንና ግጭትን ለመቀስቀስ በመጠቀም የክልሉን ሰላም ለማደፍረስ በሚሰሩ አካላት ላይ ህጋዊ አስተማሪ ዕርምጃዎችን በመውሰድ የህግ የበላይነትን በሁሉም መስክ በሙላት ለማረጋገጥ መስራት ይገባል ነው ያሉት። ኢኮኖሚው ከሚያመነጨው ገቢ ፍታሃዊ ግብር በመሰብሰብ የልማት ስራዎችን በራስ አቅም ለመሸፈን መስራት የሁሉም የጋራ ኃላፊነት በመሆኑ ገቢ አሰባሰብ ስራዎችን በማገዝ ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑንም ገልጸዋል። ሀገር በቀል የሰላም ግንባታ ተቋማትንና ህዝባዊ አቅሞችን በአግባቡ በመጠቀም በቀጣይም የክልሉን ሰላም ለማፅናት መስራት እንደሚገባም አክለዋል። በአጠቃላይ የፖሊስ ሀይሉ ከተሰጠው በላይ በመስራትና ከሚጠበቀው በላይ ፈፅሞ በመገኘት በታሪክ ተወዳሽ ለመሆን ሀላፊነቱን በአግባቡ መወጣት እንደሚገባ አቅጣጫዎች ማስቀመጣቸውም ተገልጿል።
ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደርን ተቀብለው አነጋገሩ
Mar 26, 2025 83
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አቭርሃም ንጉሤን(ዶ/ር) በፅህፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ። ውይይታቸው የኢትዮጵያን እና የእስራኤልን ትብብር ይበልጥ ማጠናከር ላይ ያተኮረ መሆኑ ተገልጿል።   በኢትዮጵያ የእስራኤል አምባሳደር አቭርሃም ንጉሤ(ዶ/ር) ከፕሬዝዳንት ታዬ ጋር የነበራቸውን ውይይት በተመለከተ ለኢዜአ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። በውይይታችን የኢትዮጵያ እና እስራኤል ግንኙነት ልዩ፣ ጥልቅ እና ታሪካዊ መሆኑን አንስተናል ብለዋል። ሁለቱ ሀገራት በኢኮኖሚ፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በደን ልማት፣ በቴክኖሎጂ፣ በግብርና፣ በሞደርናይዜሽን እና በጤና ዘርፎች በትብብር እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም እስራኤል ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዘርፈ ብዙ የሁለትዮሽ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር በቁርጠኝነት እንደምትሰራ አረጋግጠዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ የስራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁትን በኢትዮጵያ የባንግላዲሽ አምባሳደር አሰናበቱ
Mar 26, 2025 68
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- የኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ የስራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁትን በኢትዮጵያ የባንግላዲሽ አምባሳደር ሲክደር ቦዲሩዝማንን አሰናበቱ። አምባሳደር ሲክደር ቦዲሩዝማን በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ በነበራቸው ቆይታ እጅግ ደስተኛ እንደነበሩ አንስተዋል። ኢትዮጵያ ታሪካዊና ቀደምት ሀገር መሆኗን ገልጸው፤ በቆይታቸው ኢትዮጵያውያን እንግዳ ተቀባይ መሆናቸውንና ሀገሪቱም ለኑሮ ተስማሚና ምቹ መሆኗን ተመልክቻለሁ ብለዋል።   ኢትዮጵያ የአፍሪካ ማዕከል ነች ያሉት አምባሳደሩ፤ የአፍሪካ ህብረት መስራች መሆኗን ገልጸዋል። ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ የሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ባለቤት መሆኗና የዲፕሎማሲ ማዕከልነቷ የዚሁ ማሳያ ነው ብለዋል። በመሆኑም ባንግላዲሽ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ በማሸጋገር ያላቸውን ታሪካዊ ግንኙነት ለማጠናከር ቁርጠኛ አቋም እንዳላትም አረጋግጠዋል። በቆይታቸውም የሁለቱን ሀገራት ታሪካዊ ግንኙነት የሚያጠናክሩ ተግባራት ማከናወናቸውን ገልጸዋል። ለአብነትም በኢኮኖሚና በህዝብ ለህዝብ ትስስርና መሰል ተግባራት አበረታች ውጤቶች ተመዝግበዋል ነው ያሉት። በቀጣይም የባንግላዲሽና የኢትዮጵያ ግንኙነት ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል ብለዋል።
በለውጡ በተወሰዱ እርምጃዎች በሠላም ግንባታ ዘርፍ በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸው ተገለጸ
Mar 26, 2025 73
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፦በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በለውጡ በተወሰዱ እርምጃዎች አማካኝነት በሠላም ግንባታ ዘርፍ በርካታ ውጤቶች መመዝገባቸውን የክልሉ ሰላምና ጸጥታ አስተዳደር ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ኃላፊ አቶ አንድነት አሸናፊ በወቅታዊ ሁኔታ በሰጡት መግለጫ በክልሉ የታየው አዎንታዊ ሠላም ሀገር በቀል እሳቤዎችን መሰረት ያደረገ የግጭት አፈታት ስልት የመጠቀማችን ውጤት ነው ብለዋል። ባለፉት ጊዜያት በኢትዮጵያ የተሳሳቱ ትርክቶችን በማረም ወንድማማችነትንና እህትማማችነትን በሚያጎለብት መልኩ ዘላቂና አዎንታዊ ሠላም እንዲገነባ ብዙ ስራ መሰራቱን አንስተዋል ። ክልላችንም በአዲስ መልክ ከተዋቀረ ጊዜ ጀምሮ በሠላምና ፀጥታ ዘርፍ በርካታ ስራዎችን ሰርተናል ብለዋል አቶ አንድነት አሸናፊ። ክልሉ ሲመሠረት በአብዛኛዎቹ አካባቢዎች የሰላም ሁኔታ አስቸጋሪ እንደነበረና በአንዳንድ የክልሉ አካባቢዎች ደግሞ ችግሩ ከፍ ያለ እንደነበረም ጠቅሰዋል። ባለፉት ሶስት ዓመት ተኩል የሠላምና ፀጥታ ስራ በመከናወኑ ተጨባጭ ለውጦች መመዝገባቸውን አስረድተዋል። በክልሉ በምዕራብ ኦሞ፣ የሸካና የቤንች ሸኮ ዞኖች የተፈጠረውን ግጭትን፣ ሞትና መፈናቀልን ለማስቆም በዋናነት ትኩረት ተደርጎ የተሰራበት መሆኑንና የተስተጓጎሉ የህዝብ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተግባራትና የመንግሥት የስራ እንቅስቃሴዎች ዳግም ወደ ስራ እንዲገቡ የማድረግ ስራ በሰፊው መሠራቱን ጠቁመዋል፡፡ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ በክልሉ በሁሉም አካባቢዎች ህዝቡ በሠላም ወጥቶ በሠላም የሚገባበት ሁኔታ ተፈጥሯል ብለዋል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት ግጭቶችን ሙሉ በሙሉ ማስቆም ተችሏል ያሉት ኃላፊው በህዝቦች ዘንድ የነበረው ትስስር፣ አንድነት እና ወንድማማችነት እንዲጎለብት መሰራቱን ጠቅሰዋል፡፡ ለዚህም የህዝቡ ማህበራዊ እሴቶች ሀገር በቀል የግጭት አፈታት ዘዴዎች እንዲሁም የሀገር ሽማግሌዎች ሚና በእጅጉ ከፍተኛ ስለመሆኑ መግለጻቸውን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ቢሮ መረጃ ያመለክታል። በክልሉ ይቅርታ ማድረጊያ መንገዶችን በመለየትና ጫካ የገቡ አካላት ትጥቆቻቸውን በመፍታት በሠላማዊ መንገድ እጅ እንዲሰጡ በማድረግ፤ በባህላዊ መንገድ ይቅርታ ተደርጎላቸው የተለያዩ ስልጠናዎችን ወስደው ሰላማዊ ህይወት እንዲጀምሩ መደረጉን ገልጸዋል። አሁን ባለንበት ሁኔታ የህዝቦች የወንድማማችነት እና የእህታማማችነት እሳቤ ጎልብቶ በሁሉም አካባቢ ሠላም እንዲረጋገጥ ተደርጓል ብለዋል፡፡
በኦሮሚያ ክልል በአዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት ቀልጣፋ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን ነዋሪዎች ተናገሩ
Mar 26, 2025 75
ጭሮ፣ ጅማ፣ ነቀምቴ መጋቢት 17/2017 (ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በአዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት ቀልጣፋ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን የተለያዩ አካባቢ ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ የኦሮሚያ ክልል በተያዘው በጀት ዓመት አዲስ የቀበሌ አደረጃጀት ዘርግቶ ህዝቡ በአቅራቢያ የተሻለ የመንግስት አገልግሎት ማግኘት እንዲችል ማድረጉ ይታወቃል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ማብራሪያ እና ምላሽ በሰጡበት ወቅት በኦሮሚያ ክልል የተደራጁ የቀበሌ መዋቅሮች ለተሻለ አገልግሎት እየተጠናከሩ መሆኑን ተናግረዋል። ኢዜአ በምዕራብ ሀረርጌ ዞን ጭሮ ከተማ፣ ጅማ እና ምስራቅ ወለጋ ዞን ነቀምቴ ከተማ በአዲስ መልክ የተዋቀሩ የቀበሌ መዋቅሮች እየሰጡ ያሉትን አገልግሎት በተመለከተ ቅኝት አድርጓል። በዚህም ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡት የጭሮ ከተማ ነዋሪዎች እንዳሉት ከዚህ ቀደም እስከ ሁለት ቀን ወደ ወረዳ ማእከል በመመላለስ ሲያገኙ የነበረውን አገልግሎት በቀበሌ ደረጃ በሰአታት ውስጥ እያገኙ ነው፡፡ አስተያየታቸውን ከሰጡን መካከል የጨፌ አራራ ቀበሌ ነዋሪና የኦዳ ቡልቱም ዩኒቨርስቲ ሰራተኛ የሆኑት ወይዘሮ ሀረገወይን ተገኔ አንዷ ሲሆኑ ለመኖርያ ቤት እድሳት ወደ ቀበሌ መምጣታቸውን ገልፀው ጉዳያቸው በሰዓታት ውስጥ እንደተፈጸመላቸው ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም ለመኖሪያ ቤት እድሳት ወደ ከተማው አስተዳደር በመመላለስ ከሁለትና ሶስት ቀናት በላይ እንደሚያጠፉም ነው የተናገሩት። በመሬት ይዞታ ልኬትና በወሰን ማስተካከል ጉዳይ በቀበሌ ደረጃ አገልግሎት እንዳገኙ የተናገሩት ወይዘሮ ውባለም መንግስቱ ሲሆኑ ከዚህ ቀደም በከተማ አስተዳደር ደረጃ አገልግሎቱ ሲሰጥ ለቀናት የመመላለስ ችግር ነበር ያሉት አስተያየት ሰጪዋ ''ይህም ጊዜያችንን ሲያባክንብን ነበር'' ብለዋል፡፡ በጅማ ዞንም በተመሳሳይ በቀበሌ ደረጃ የተዋቀሩ አደረጃጀቶች ህዝቡን በቅርበት እያገለገሉ መሆኑን ተገልጋዮች ተናግረዋል። ከነዋሪዎቹ መካከል በዞኑ የናዳ ወረዳ የመረዋ ቀበሌ ነዋሪ አባ ጀበል አባ ወሊ፤ ''የቀበሌ አደረጃጀቱ ለችግሮቻችን መፍትሔ ለመስጠት እና የተለያዩ አገልግሎቶችን እንድናገኝ አግዞናል'' ብለዋል። በተለይም የቀበሌ አደረጃጀቱን ተከትሎ የተለያዩ የመሰረተ ልማቶች እየተስፋፉ መሆኑን ጠቅሰው በዚህም ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን አስረድተዋል። ሌላው ነዋሪ አባ ረሻድ አባ ቢያ በበኩላቸው ከዚህ በፊት አገልግሎት ለማግኘት ወረዳ ማእከል ድረስ በመሄድ የትራንስፖርት ወጪና የድካም እና እንግልት ሲደርስባቸው እንደቆየ አንስተዋል። በተመሳሳይ አዲስ የተዘረጋው የቀበሌ አደረጃጀት አገልግሎት አሰጣጥ ሂደቱን ያሳለጠ እና ተጠቃሚ ያደረጋቸው መሆኑን የነቀምቴ ከተማ ነዋሪዎች ተናግረዋል። የነቀምቴ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ ስኳሬ ቀጄላ፤ የከተማዋ ነዋሪዎች በቀበሌ ደረጃ በተዘረጋው የአገልግሎት አሰጣጥ ያለ እንግልት በመገልገል ላይ እንደሚገኙ ገልፀዋል። የቀበሌ መዋቅሩ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የህብረተሰቡ ክፍሎች ትኩረት ማግኘት መቻላቸውን በማንሳት በተለይ ዜጎች በመደራጀት ገቢያቸውን እንዲያሳድጉ፣ የመኖሪያ ቤት እንዲያገኙ እና ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉን አንስተዋል። ሌላኛዋ የከተማዉ ነዋሪ ወይዘሮ ለሊሴ ነጋሳ ከዚህ በፊት መታወቂያ ለማግኘት አስቸጋሪ እንደነበረ ጠቅሰው ዛሬ ላይ ግን የሚያስፈልገውን ሂደት በሟሟላት ብቻ ነዋሪዎች የሚፈልጉትን እያገኙ መሆኑን ተናግረዋል። በነቀምቴ ከተማ የቡርቃ ጃቶ ቀበሌ አስተዳደሪ አቶ መልካሙ ቡልቲ፤ በቀበሌ መዋቅሩ የተገልጋዩን እንግልት ለመቀነስ የእረፍት ቀናትን ጨምሮ እየተሰራ ይገኛል ብለዋል። መዋቅሩ የመሰረተ ልማት ስራዎችን ማሻሻል፣ በኢንቨስትመንት ተይዘው ለረዥም አመታት ያልለሙ ቦታዎችን ለወጣቶች በማስረከብ፣ የህብረተሰቡን ጥያቄዎች በቅርበት በመረዳት እና ያለአግባብ የሆኑ ወጪዎችን በመቀነስ ዘርፍ ብዙ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል።   የጭሮ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ጀማል ጎሳዬ አንዳሉት በአዲሱ የቀበሌ አደረጃጀት በከተማው የሚገኙ አስሩም ቀበሌዎች ከ100 በላይ አዳዲስ ባለሙያዎች ለህብረተሰቡ በቅርበት አገልግሎት እንዲሰጡ ተመድበዋል። የከተማ አስተዳደሩ በአመቱ አገልግሎቱን ለማጠናከር ከ16 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የሁለት የቀበሌ ፅህፈት ቤቶች ግንባታ እያከናወነ መሆኑን ገልጸው ሁሉንም የቀበሌ ጽህፈት ቤቶች በቁሳቁስ በማሟላት ለህብረተሰቡ ፈጣን አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉንም ነው አቶ ጀማል የተናገሩት፡፡   የጅማ ዞን ምክትል አስተዳዳሪ አቶ የሱፍ ሻሮ፤ በዞኑ ህዝቡ በቀበሌ ደረጃ አስፈላጊ አገልግሎት መጠቀም እንዲችል በሁሉም ቀበሌዎች መዋቅር እየተዘረጋ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ 562ቱ ቀበሌዎች አደረጃጀቱ በትኩረት እየተተገበረ ሲሆን ህዝቡም ጥሩ ግብረ መልስ እየሰጠ መሆኑን አመልክተው ለሁሉም ቀበሌዎች የአስተዳደር ባለሙያዎች ተመድበው ስራ ላይ ይገኛሉ ብለዋል።  
በሐረሪ ክልል በለውጡ ዓመታት ህዝቡን የሰላም ባለቤት በማድረግ አበረታች ውጤት ተመዝግቧል
Mar 26, 2025 68
ሐረር፤ መጋቢት 17/2017 (ኢዜአ)፡- በሐረሪ ክልል በለውጡ ዓመታት ህዝቡን የሰላም ባለቤት በማድረግ በተከናወኑ ተግባራት አበረታች ውጤት መመዝገቡን የክልሉ ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ጉዳዮች ቢሮ አስታወቀ። የቢሮው ሃላፊ አቶ ተውፊቅ መሀመድ በክልሉ ባለፉት ሰባት የለውጥ ዓመታት ሰላምና ጸጥታን ከማረጋገጥ አንጻር የተከናወኑ ስራዎችና የተገኙ ውጤቶችን በተመለከተ መግለጫ ሰጥተዋል። አቶ ተውፊቅ በመግለጫቸው እንዳስታወቁት በክልሉ ባለፉት ሰባት የለውጥ ዓመታት ህዝቡን የሰላም ባለቤት በማድረግ በተከናወነው ስራ አበረታች ውጤት ተመዝግቧል ። "በዘርፉ ህዝቡን በማሳተፍ የተከናወነው ስራ ጉልህ ሚና አበርክቷል " ብለዋል። በክልሉ መንግሥትም መልካም አስተዳደር የማስፈንና የሕግ የበላይነትን የማረጋገጥ ስራ በትኩረት መከናወኑን አመልክተዋል። በክልሉ አስተማማኝ ሰላም በመረጋገጡ በህዝብና በመንግስት ትብብር በከተማና በገጠር በርካታ የልማት ስራዎች መከናወናቸውን ተናግረዋል። በተጨማሪም በህዝቦች መካከል አብሮነት የጎለበተበት፣ እህትማማችነትና ወንድማማችነት የዳበረበት መሆኑን ጠቅሰዋል ። የተገኘው ውጤት የለውጡ ትሩፋት መሆኑን የጠቀሱት አቶ ተውፊቅ በተለይ የሃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ የአባ ገዳዎች አስተዋጾ ከፍተኛ መሆኑን አስታውቀዋል።
ለፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት የተሟላ ትግበራ የመንግስትን ጥረት በማገዝ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም መገንባት ይገባል
Mar 26, 2025 77
መቀሌ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፦ ለፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት የተሟላ ትግበራ የፌዴራል መንግስትን ጥረት በማገዝ በትግራይ ክልል ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም መገንባት እንደሚገባ ተገለጸ። በሰሜን ኢትዮጵያ የነበረው ጦርነት በፕሪቶሪያ በተደረሰው የሰላም ስምምነት እልባት በማግኘቱ በክልሉ ባለፉት ሁለት ዓመታት ሰላምና መረጋጋት መፈጠሩ ይታወቃል። ከሰላምና መረጋጋት ባለፈም በክልሉ ተቋርጠው የነበሩ የማህበራዊ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት በአፋጣኝ ወደ ስራ እንዲመለሱ በማድረግ የፌዴራሉ መንግስት ተጨባጭ ስራዎች የተስተዋሉበትም ነው። በክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር ተቋቁሞ የሰላም፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ሲሰራና በስምምነቱ መሰረትም የተለያዩ ተግባራትን ሲያከናውን ቆይቷል። በክልሉ የቀድሞ ታጣቂዎች ትጥቃቸውን ፈትተው ለሀገር መከላከያ በማስረከብ በተሃድሶ ኮሚሽን በኩል ስልጠና ወስደው በዘላቂነት ማቋቋም እንደሚገባም ስምምነቱ ያስገድዳል። ይሁን እንጂ የትጥቅ ማስፈታት ሂደቱ እስካሁን በሚፈለገው ልክ አለመከናወኑ ለሰላም ሂደቱ እንከን የሚፈጥር መሆኑን ኢዜአ ያነጋገራቸው የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ተናግረዋል። በመሆኑም ለፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት የተሟላ ትግበራ የመንግስትን ጥረት በማገዝ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም መገንባት ይገባል ሲሉ ገልጸዋል። በዩኒቨርሲቲው የእንስሳት ህክምና ኮሌጅ ዲን አብርሃም ብስራት(ዶ/ር)፤ የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት በተለይም ለክልሉ ህዝብ የሰላም መሰረት መሆኑን ተናግረዋል። በመሆኑም የሰላም ስምምነቱን ለመተግበር የፌዴራል መንግስት ያሳየውን ቁርጠኝነት አድንቀው ሌሎችም የድርሻቸውን ኃላፊነት መወጣት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። የስምምነቱን ሂደት መተግበር ከምንም በላይ ለትግራይ ክልል ህዝብ ዘላቂ ሰላምና ልማት መሰረት የሚያኖር መሆኑን አንስተው የሰላም ጉዳይ ለሁሉ ነገር ወሳኝ በመሆኑ ለዚሁ በቁርጠኝነት መስራት ይገባል ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል። የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት በክልሉ ጦርነትን ከማስቆምም ባለፈ በወቅቱ የነበሩትን ውስብስብ ችግሮች መፍታት ያስቻለ ሁነኛ መፍትሄ መሆኑንም ተናግረዋል። በመሆኑም ለፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት መሳካት የፌዴራል መንግስትን ጥረት በማገዝ በክልሉ ዘላቂና አስተማማኝ ሰላም መገንባት ይገባል ብለዋል። በዩኒቨርሲቲው መምህርና ተመራማሪ ዮሃንስ ተኽለ (ዶ/ር)፤ ከምንም በላይ ለሰላም የሚከፈል ዋጋ ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን ገልጸዋል። የፕሪቶሪያው የሰላም ስምምነት ዘላቂ እንዲሆን የመንግስት ጥረት እንዳለ ሆኖ የልሂቃን፣ ምሁራን፣ የሲቪክ ማህበራት እና አጠቃላይ የህዝቡ ጥረትና ተሳትፎ ወሳኝ መሆኑንም አንስተዋል። በዩኒቨርሲቲው የድህረ ምረቃ አስተባባሪ ንጉስ አበበ(ዶ/ር)፤ የሰላም ጉዳይ የሁሉም ነገር መሰረት በመሆኑ ለቀጣይነቱ በጋራ መስራት ይገባል ሲሉም ተናግረዋል። የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዝዳንት ጌታቸው ረዳ መጋቢት 4 ቀን 2017 ዓ.ም በሰጡት መግለጫ ለክልሉ ዘላቂ ሰላምና ልማት የፌዴራሉ መንግስት ያደረገውን ጉልህ አስተዋጽኦ አድንቀዋል። የትግራይ ክልል ህዝብ ሰላምን፣ ልማትንና መረጋጋትን እንደሚሻ አንስተው፤ የግጭት አባዜ ያለበትን ቡድን ህዝቡ መታገልና አደብ ማስገዛት አለበት ማለታቸው ይታወሳል።
በድሬዳዋ የህዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው ይቀጥላሉ
Mar 26, 2025 49
ድሬዳዋ፤ መጋቢት 17/2017(ኢዜአ)፡- በድሬዳዋ አስተዳደር የነዋሪዎችን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት የሚከናወኑ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የአስተዳደሩ ከንቲባ የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ ሰይፉ ታደሰ(ዶ/ር) ተናገሩ። በድሬዳዋ የብልጽግና ፓርቲ አባላት ዛሬ በለውጡ ዓመታት የተገኙ ውጤቶችን ማስቀጠል የሚያስችል ውይይት አካሂደዋል።   ውይይቱን የመሩት የከንቲባው የማህበራዊ ዘርፍ አማካሪ ሰይፉ ታደሰ(ዶ/ር) እንደተናገሩት፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በማህበራዊ፣ በኢኮኖሚና በፖለቲካው ዘርፎች ተስፋ ሰጪ ውጤቶች ተመዝግበዋል። በየተቋማቱ ዲጂታል አሰራሮችን በመዘርጋት ለህብረተሰቡ ፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ተደራሽ ተደርገው የህዝብ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች እየተመለሱ መሆናቸውን ለአብነት አንስተዋል። እየተመዘገቡ ለሚገኙ የለውጥ ውጤቶችም የብልጽግና ፓርቲ አባላት ግንባር ቀደም ተሳትፎ ወሳኝ አበርክቶ እንዳለውም ተናግረዋል። እነዚህን የለውጥ ውጤቶች ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር አባላቱ እያደረጉ የሚገኙትን ርብርብ አጠናክረው እንዲቀጥሉም አስገንዝበዋል። የአስተዳደሩ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ ብሩክ ፈለቀ በበኩላቸው አሰባሳቢ የጋራ ትርክቶችንና የጋራ ማንነትን በማነፅ በኩል ነዋሪው በየመስኩ የሚያደርገው ተሳትፎ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በትኩረት እየተሰራ ነው ብለዋል። ፈጣንና ትክክለኛ መረጃዎችን ለህብረተሰቡ ተደራሽ በማድረግ የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ይበልጥ እንዲጎለብቱ ትኩረት መሰጠቱን በመግለፅ። የተጀመሩትን የልማት ስራዎች በቅንጅት ማሳካት የድሬዳዋን ከፍታ ለማረጋገጥ ወሳኝ ነው ያሉት ደግሞ የውይይቱ ተሳታፊ አቶ ካሊድ አህመድ ናቸው። ከተረጂነት ወደ አምራችነት እየተደረገ የሚገኘውን ጉዞ ለማፋጠን የብልጽግና ፓርቲ አባላት ከመቼውም ጊዜ በላይ ኃላፊነታችንን እንወጣለን ብለዋል።
ለገዢ ትርክት ግንባታ የሚያግዝ ዘመኑን የዋጀ የሚዲያና የህዝብ ግንኙነት አሰራር ያስፈልጋል
Mar 26, 2025 62
ወልቂጤ፤ መጋቢት 17/2017 (ኢዜአ):- ለገዢ ትርክት ግንባታ የሚያግዝ ዘመኑን የዋጀ የሚዲያና የህዝብ ግንኙነት አሰራር መቅረጽ እንደሚያስፈልግ በብልጽግና ፓርቲ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ዲላሞ ኦቶሬ (ዶ/ር) ገለጹ። "ውጤታማ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን ለገዢ ትርክት" በሚል መሪ ሃሳብ ለሚዲያና ኮሙኒኬሽን አመራሮችና ባለሙያዎች እየተሰጠ የሚገኘው ስልጠና እንደቀጠለ ነው። በዛሬው የሶስተኛ ቀን ውሎው ስልጠናው ''መሰረታዊ የመሪነት ጥበብ እና አገልጋይ መሪ'' በሚል መሪ ሀሳብ ነው እየተሰጠ የሚገኘው። ስልጠናውን የሚሰጡት በብልጽግና ፓርቲ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ዲላሞ ኦቶሬ (ዶ/ር ) እንዳሉት ለገዢ ትርክት ትኩረት የሚሰጥ የሚዲያና የህዝብ ግንኙነት አመራርና ባለሙያ ለመገንባት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ ነው። ሚዲያው ለህዝብ ጥቅም የሚሆኑ ገዢ ትርክቶችን እያጎለበተ በሚያስተሳስሩ አጀንዳዎች ላይ ማተኮር እንዳለበት አንስተው ይህም ሀገራዊ የልማትና ሁለንተናዊ ብልጽግና ግቦችን ለማሳካት አበርክቶ ይኖረዋል ብለዋል። ዘርፉ ለተግባቦት ቅድሚያ የሚሰጥ እንዲሁም ለልማት የሚያነሳሳ ሲሆን ለሀገር ልእልና ያለው ፋይዳም ትልቅ ነው ብለዋል። ለዚህም በተገቢው መምራትና ማብቃት እንዲሁም ዘመኑን የዋጀ ለገዢ ትርክት የሚያግዝ አሰራር መቅረጽ እንደሚያስፈልግም ተናግረዋል። መረጃን በወቅቱና በኃላፊነት ለህዝብ ተደራሽ ማድረግ ትልቅ ተልዕኮ አንግቦ የሚሰራ ሊሆን ይገባል ያሉት ኃላፊው የጋራ አጀንዳና መልዕክት ቀርጾ ለሀገረ መንግሥትና ተቋም ግንባታ የበኩሉን ማበርከት ይኖርበታል ሲሉም ተናግረዋል። በክልሉ ዘርፉን ለማሳደግና ተቋማዊ ግንባታን ለማጎልበት በልዩ ሁኔታ እየሰራ መሆኑን የጠቆሙት የጽህፈት ቤት ኃላፊው የዘርፉ አመራርና ባለሙያ ይህን ታሳቢ አድርጎ ራሱን በክህሎት ማብቃት እንደሚጠበቅበትም አመልክተዋል። በስልጠናው መድረክ የክልሉ መንግሥት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ ዘሪሁን እሸቱ እና የክልሉ አመራር አካዳሚ ኃላፊ አቶ ተስፋዬ ብላቱን ጨምሮ በየደረጃው የሚገኙ የሚዲያ እና ኮሙኒኬሽን እንዲሁም የማህበረሰብ ሬድዮ እና ቴሌቪዥን አመራር አባላት እየተሳተፉ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በትግርኛ ቋንቋ ያስተላለፉት መልዕክት
Mar 26, 2025 132
ጻውዒት ጥቆማ ፕረዚደንት ጊዝያዊ ምምሕዳር ትግራይ ንመላእ ህዝቢ ትግራይ ከምዝፍለጥ በመሰረት ሕገ መንግስቲ ፈዴሪኢ 62(9)፣ ከምኡውን በመሰረት ስምምዕነት ፕሪቶሪያን ኣብ ክልላት ምእታው ጣልቃ መንግስቲ ፈዴራል ንምድንጋግ ብዝወጸ አዋጅ ቁጽሪ 359/1995 መሠረት፣ ከምኡውን ምምስራት ኣሳታፊ ግዚያዊ ምምሕዳር መንግስቲ ትግራይ ብዝምልከት ዝተደንገገ ናይ ቤት ምኽሪ ሚንስተራት ደንቢ ቁጥር 533/2015 መሠረት ዝቆመ ጊዚያዊ ምምሕዳር ትግራይ ንክልተ ዓመታት ኣብ ስራሕ ምጽንሑ ይፍለጥ። በመሰረት ኣወጅ 359/1995 ኣንቀጽ 15(3) ጊዚያዊ ምምሕዳር ንክልተ ዓመት ጥራይ እዩ ክጸንሕ ዝኽእል። ጭቡጥ ምክንያት እንተሃልዩ ግና ዕድመ እቲ ጊዚያዊ ምምሕዳር ምንዋሕ ይከኣል። በቶም ቅድም ክብል ዝተገለጹ ሕግታትን ውዕሊ ፕሪቶሪያ ዝቆመ ጊዝያዊ ምምሕዳር ትግራይ ኣብ ውሽጢ ኽልተ ዓመት ናይ ጊዝያዊ ምምሕዳር ዕማማቱ አጻፊፉ ሓላፍነቱ ብህዝቢ ንዝተመረጸ መንግስቲ ከረክብ ይግባእ ነይሩ። ይኹን እንበር ጊዝያዊ ምምሕዳር ትግራይ ዝተውሃቦ ቁልፊ ዕማማት ኣብ ዝተወሰነሉ ጊዜ ከጻፍፍ ኣይከኣለን። ካብቶም ቁልፊ ዕማማት ሓድ ምርጫ ንምከያድ ዘኽእል ምቹእ ኩነታት ምፍጣር እዩ። እዙ ዕማም እዙይ ካብቶም ዘይተጻፈፉ ዕማማት ሓደ ብምዃኑ ዕድመ ጊዝያዊ መንግስቲ ሕጊ ብምምሕያሽ ብሓደ ዓመት ምንዋሕ ግድን ኰይኑ አሎ። መንግስቲ ፈዴራል ኣብ መሬት ዘሎ ጭቡጥ ኩነታት ኣብ ግምት ብምእታው ዕደመ ጊዚያዊ መንግስቲ ንምንዋሕ፣ ፖለቲካዊ፣ ምምሕዳራውን ናይ ሕግን ስራሕቲ ኣብ ምክንዋን ዝርከብ ኰይኑ ምስእዙይ ተኣሳሲሩ ሓዱሽ ፕረዚደንት ጊዝያዊ ምምሕዳር ምሻም እውን ኣድላይ ኰይኑ አሎ። ከም ዝፍለጥ በመሰረት ደንቢ ቁጽሪ 533/2015 አንቀጽ 3(2) ፕረዚደንት ጊዚያዊ ምምሕዳር ምሻም ናይ ቀደማይ ሚስትር ሓላፍነት እኳ እንተኮነ ህዝቢ ብዝተማለአ መገዲ ብምርጫ መራሕቱ ክሳብ ዝመርጽ ኣብ ጥቆማ ፕረዚደነት ጊዝያዊ ምምሕዳር ተሳትፎ ክህልዎ ኣድላይ ብምኳኑ፤ ንዕማማት ጊዝያዊ ምምሕዳር ብብቕዓት ክፍጽሙ ይከእሉ እዮም ፣ ሰላምን ድሕንነትን እቲ ክልል ከራጋግፁ ይከእሉ እዮም ትብልዎም ሕጹያት ኣብታሕቲ ናብ ዝተገለጸ ናይ ቀደማይ ሚነስትር ቢሮ ኢሜል አደራሻ ከብ ሎሚ ጀሚርኩም ጥቆማኹም ክትልእኹ ከምትኽእሉ ነፍልጥ። መጠቆሚ ኢመይል info@pmo.gov.et
ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲያዊ ጥረት እና በሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች ለአፍሪካ የጋራ ደህንነት እና ለዓለም ሰላም መረጋገጥ ያላትን ቁርጠኝነት  በተግባር አሳይታለች
Mar 25, 2025 56
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 16/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲያዊ ጥረቷ እና በሰላም ማስከበር ተልዕኮዎቿ ለአፍሪካ የጋራ ደህንነት እና የዓለም ሰላም መረጋገጥ ያላትን ቁርጠኝነት በተግባር ማሳየቷን አምባሳደር ሂሩት ዘመነ ገልጸዋል። በአፍሪካ ህብረት እና በተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን(ኢሲኤ) የኢትዮጵያ ቋሚ መልዕክተኛ አምባሳደር ሂሩት ዘመነ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ እና ለዓለም ሰላም መከበር ያላትን የጸና መሻት ከቃል ባለፈ በሰላም ማስከበር ተልዕኮ እና በዲፕሎማሲ ጥረቶቿ በተግባር አሳይታለች ብለዋል። ኢትዮጵያን ጨምሮ የአፍሪካ ህብረት የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት አዲስ ተመራጭ አባል ሀገራትን የመቀበል ስነ-ስርዓት ዛሬ በታንዛንያ አሩሻ ከተማ መካሄድ ጀምሯል። በአምባሳደር ሂሩት ዘመነ የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ በስነ-ስርዓቱ ላይ እየተሳተፈ ይገኛል። በመድረኩም አምባሳደር ሂሩት የአፍሪካ ህብረት ኢትዮጵያ የምክር ቤቱ አባል እንድትሆን ለሰጠው ድጋፍ አመስግነዋል። ኢትዮጵያ በዲፕሎማሲያዊ ጥረቷ እና በሰላም ማስከበር ተልዕኮዎቿ ለአፍሪካ የጋራ ደህንነት እና የዓለም ሰላም መረጋገጥ ያላትን ቁርጠኝነት እና ድጋፍ በተግባር ማሳየቷን ገልጸዋል።   የቀውስ ሁኔታዎች ወደ ግጭቶች እንዳያመሩ የቅድመ ማስጠንቀቂያ እና ምላሽ ስርዓትን ማጠናከር እንዲሁም የግጭት መከላከያ አማራጮችን በመተግበር ሰላምን ማጽናት እንደሚገባ አመልክተዋል። አምባሳደር ሂሩት አሁን ካለው አህጉራዊ ወቅታዊ ሁኔታ አንጻር የምክር ቤቱን የፋይናንስ አቅም ዘላቂነት እና ውጤታማነት በሚያረጋግጥ መልኩ መደገፍ ወሳኝ መሆኑን ተናግረዋል። ምክር ቤቱ የዓለም ተለዋዋጭ የጂኦ ፖለቲካዊ ሁኔታ ውስጥ በአፍሪካ እና በተቀረው ዓለም ላይ የፈጠረውን ነባራዊ እውነታ በውል የተገነዘበ ዝግጅት በማድረግ በአህጉሪቱ የጋራ ፍላጎት ውስጥ ትርጉም ያለው ሚና መጫወት ይኖርበታል ነው ያሉት። በስነ ስርዓቱ ላይ የአፍሪካ ህብረት የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት አዲስ አባላት ኢትዮጵያ እና ኢስዋቲኒ አቀባበል ተደርጎላቸዋል። በድጋሚ አባል ሆነው የተመረጡት ካሜሮን እና ናይጄሪያም በሁነቱ ላይ ተገኝተዋል።   ኢትዮጵያ በምክር ቤቱ በማርች 2025 በታዛቢነት እያገለገለች ሲሆን ከእ.አ.አ አፕሪል ወር 2025 አንስቶ በይፋ በአባልነት ማገልገል እንደምትጀምር ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመለክታል። በታንዛንያ አሩሻ የሚካሄደው የአቀባበል እና ልምድ ልውውጥ መርሃ ግበረ እስከ መጋቢት 18 ቀን 2017 ዓ.ም ይቆያል። የአፍሪካ ህብረት የስራ አስፈጻሚ ምክር ቤት በየካቲት ወር 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ባደረገው 46ኛ መደበኛ ስብሰባ አራት የህብረቱን የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት አባላት መምረጡ ይታወቃል። በዚህም ኢትዮጵያ ከምስራቅ አፍሪካ፣ ኢስዋቲኒ ከደቡባዊ አፍሪካ፣ ካሜሮን ከማዕከላዊ አፍሪካ እና ናይጄሪያ ከምዕራብ አፍሪካ አባል ሆነው መመረጣቸው የሚታወስ ነው። ኢትዮጵያ የአፍሪካ ሕብረት የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት የእ.አ.አ 2025 እስከ 2027 የቆይታ ዘመን አባል ሆና ተመርጣለች። 21 ዓመታትን ያስቆጠረው የአፍሪካ ህብረት የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት በአህጉሪቱ ግጭቶች እንዳይከሰቱ አስቀድሞ መከላከል፣ የግጭት አስተዳደርና አፈታት ላይ ከፍተኛ የውሳኔ ሰጪ አካል ነው።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም