አካባቢ ጥበቃ
የኮሪደር ልማት ሰራው የመዲናዋን አረንጓዴ ሽፋን ለማሳደግ ሚናው የጎላ ነው - የአዲስ አበባ ከተማ ውበት እና አረንጓዴ ልማት ቢሮ
Apr 20, 2024 81
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 12/2016 (ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ ከተማ እየተከናወነ ያለው የኮሪደር ልማት ስራ የመዲናዋ አረንጓዴ ሽፋን ለማሳደግ ሚናው የጎላ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ውበት እና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ገልጿል። የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪዎች ቁጥር እያደገ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ የመሰረተ ልማት ፍላጎቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመሩ መጥተዋል፡፡ ይህንንም ለዓመታት የተሻገሩ የመሰረተ ልማት ችግሮች ለመፍታት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ የኮሪደር ልማት ስራ ተጠቃሽ ነው፡፡ የኮሪደር ልማት ስራው ሲጠናቀቀም የህብረተሰቡን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ከመመለስ ባለፈ የመዲናዋን ውበትና ገጽታ የሚቀይር ነው፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ውበት እና አረንጓዴ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ይመኙሻል ታደሰ፤ ከዚህ ቀደም የሚከናወኑ የልማት ስራዎች ከአረንጓዴ ልማት ጋር የተሳሰሩ እንዳልነበሩ ተናግረዋል፡፡ ይህም ከተማዋን የሚመጥናት ገጽታን እንዳትላበስ አድርጓት መቆየቱን ነው ያነሱት፡፡ ካለፉት 5 ዓመታት ወዲህ የከተማዋን እድገት ከአረንጓዴ ልማት ጋር በማስተሳሰር ውብ ጽዱና ለዜጎቿ የምትመች ከተማ መፍጠር ላይ የተሻለ ስራ መከናወኑንም ጠቁመዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተጀመረው የኮሪደር ልማት ስራ ደግሞ የከተማዋን ውበትና አረንጓዴ ሽፋን ለመጨመር ለሚከናወኑ ስራዎች ተጨማሪ አቅም እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡ የኮሪደር ልማት ስራው በተለይ በከተማዋ መስፈርትን በጠበቀ መልኩ የአረንጓዴ አሻራ መርሀ ግብሮችን ለማከናወን ማነቆ የሆኑ ችግሮችን እንዲፈቱ ጉልህ ሚና እንደሚኖረው ነው የገለጹት፡፡ ይህም የከተማዋን የቱሪስት ፍሰትና የቆይታ ጊዜ ለማራዘም ያግዛል ነው ያሉት፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት የተከናወኑ የአረንጓዴ ልማት ስራዎች የከተማዋን የአረንጓዴ ሽፋን ከነበረበት 2 ነጥብ 8 ወደ 15 በመቶ እንዲያድግ ማድረጉን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡    
በመዲናዋ እየተተገበረ የሚገኘው የወንዞች ዳርቻ ልማት የመዲናዋን ወንዞች ትንሳኤ አብስሯል-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Apr 19, 2024 256
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016(ኢዜአ)፦ ካለፉት አምስት አመታት ጀምሮ በመዲናዋ እየተተገበረ የሚገኘው የወንዞች ዳርቻ ልማት የመዲናዋን ወንዞች ትንሳኤ ያበሰረ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ "ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ" በሚል መሪ ሃሳብ ለቀጣዮቹ ስድስት ወራት ንቅናቄ አስጀምረዋል።   ንቅናቄው የአካባቢ ብክለትን በመከላከል ጽዱ አዲስ አበባን እውን ለማድረግ አላማ የያዘ ነው፡፡ በመርኃ ግብሩ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ቡዜና አልከድር፣ የአዲስ አበባ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ስራአስኪያጅ ድዳ ድሪባ፣ የካቢኔ አባላት እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። በዚሁ ወቅት የመዲናዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ እንዳሉት፤ አዲስ አበባ እንድትመሰረት ምክንያት የሆናት የተፈጥሮ ሀብቷና መልከ ብዙ የአየር ንብረቷ ነው። ይሁን እንጂ እነዚህን የተፈጥሮ ሀብቶች በአግባቡ መጠበቅ ባለመቻሉ መዲናዋ ለከፍተኛ ብክለት ተዳርጋለች ሲሉ የችግሩን አሳሳቢነት ጠቁመዋል፡፡ እነዚህ ጉልህ ችግሮች በከተማዋና በዙሪያዋ ባሉ አካባቢዎች ጤናን የሚያውኩ ጉዳቶችን እያስከተሉ ነው ብለዋል። ይህን ተከትሎ ባለፉት አምስት ዓመታት ችግሮቹን ለማቃለልና የከተማዋን ስነ-ምሕዳር ለማሻሻል የሚረዱ ሜጋ ፕሮጀክቶች ላይ ትኩረት ተደርጎ መሰራቱን አብራርተዋል። በዋናነትም በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት እየተተገበረ የሚገኘው የወንዝ ዳርቻ ልማት የመዲናዋን ወንዞች ትንሳኤ ያበሰረ መሆኑን ጠቁመዋል። በተጨማሪም የአረንጓዴ አሻራ መርኃ ግብር በከፍተኛ ሁኔታ እየቀነሰ የነበረውን የመዲናዋን የደን ሽፋን መታደግ እንዳስቻለ አስታውቀዋል። እነዚህ ስራዎች ዘላቂ ልማትን ከማረጋገጥ አንጻር ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን አመላክተዋል። በከተማዋ ያለው የፍሳሽ ማስወገጃ ስርአት በአብዛኛው ከወንዞች ጋር የተገናኘ በመሆኑ በቅርቡ የተጀመረው የኮሪደር ልማት ችግሩን ለመፍታት እንደሚያስችል ተናግረዋል። ረጅም ጊዜ ያገለገሉ ተሽከሪዎች በአየር ንብረት ላይ አሉታዊ ተጽእኖ እያሳደሩ መሆኑን በመጠቆም በታዳሽ ሀይል የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል የወጣው ፖሊሲ የአየር ንብረት ብክለትን ለመከላከል ትልቅ ግብአት መሆኑንም አንስተዋል። የድምጽ ብክለት የከተማዋ ተጨማሪ ችግር እየሆነ መምጣቱን አንስተው ችግሩ ከተለያዩ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ አገልግሎት መስጫ ተቋማት የሚመነጭ መሆኑን አስረድተዋል። የብክለት ችግሮቹን ከመሰረቱ ለመፍታት የተጀመሩ ጥረቶችን ለማጠናከር ግንዛቤን ማሳደግ እና የተቀመጡ ህጎችና መመሪያዎችን መተግበር እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአዲስ አበባ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ስራ አስኪያጅ ድዳ ድሪባ በበኩላቸው ንቅናቄው የአካባቢ ብክለትን በመከላከል ጽዱና የበለጸገች አገር ለትውልድ የማስተላለፍ አላማ መያዙን ገልጸዋል። የአካባቢ ብክለት በአካባቢ እና በሰው ልጅ ላይ ወቅታዊና ዘላቂ ችግር እንደሚያስከትል ገልጸው አሁን የተጀመረው ንቅናቄ ቋሚ አሰራር ሆኖ እንደሚቀጥል ጠቁመዋል።  
አካባቢን ለኑሮና ለስራ ምቹ ለማድረግ ከደረቅ ቆሻሻና ፕላስቲክ ብክለት የመከላከል ንቅናቄ ይካሄዳል
Apr 19, 2024 153
ሐረር/ድሬዳዋ ፤ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ አካባቢን ለኑሮና ለስራ ምቹ ለማድረግ ከደረቅ ቆሻሻና ፕላስቲክ ብክለት የመከላከል ንቅናቄ እንደሚያካሄድ የሐረሪ ክልል አካባቢ ጥበቃ እና የድሬዳዋ አስተዳደር የአካባቢ፣ የደንና የአየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣናት አስታወቁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ ከሰሞኑ ከተሞቻችን እና አካባቢያችንን ጽዱ ለማድረግ እንተባበር ባሉት መልዕክታቸው እንደገለጹት፤ የፕላስቲክ እና የቆሻሻ ብክለት ሥነ ምህዳራችንን እና ጤናችንን አደጋ ላይ ይጥላል። ''በሃላፊነት ስሜት ቆሻሻን በአግባቡ በማስወገድ እና ዘላቂ አማራጮችን በመምረጥ ተፈጥሮን ለትውልድ ማቆየት እንችላለን'' ማለታቸው ይታወሳል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የሐረሪ ክልላዊ መንግስት እና ድሬዳዋ አስተዳደር ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሃላፊዎች ችግሩን ለመግታት በትኩረት እንደሚንቀሳቀሱ አረጋግጠዋል። በሐረሪ ክልል አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ሃላፊ አቶ ሰሚር በክሪ እንደተናገሩት፤ ባለስልጣኑ በአካባቢ ብክለት፣ ቁጥጥርና ህግን ከማስፈፀም አኳያ የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል። አካባቢው ስነ ምህዳርና ተፈጥሯዊ ይዘቱን በጠበቀ መልኩ ለህብረተሰቡ አገልግሎት እንዲሰጥ የአካባቢ ጥበቃ ስራዎችን የማጎልበት ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን በማከል። በተለይ በክልሉ ከተማና ገጠር አካባቢዎች በከባቢ አየር፣ ውሃ፣ በአፈርና በድምፅ ብክለት ደረጃዎች ላይ የተቀናጀ የክትትልና ቁጥጥር ስራ እያከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። በሐረር ከተማም ከተቋማትና ከሌሎች የሚወጡ የደረቅና ፍሳሽ ቆሻሻ አወጋገድ ጋር በተያያዘ ውስንነት እንደሚታይ የተናገሩት አቶ ሰሚር፤ ችግሩን ለመፍታት በተቀናጀ መልኩ ስራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን አመልክተዋል። በተለይም ደረቅ ቆሻሻን ከምንጩ ጀምሮ የማስወገድ ሂደቱ ስርዓቱን ጠብቆ እንዲከናወን እየተከታተለና በትክክል በማይፈጽሙት ላይ እርምጃ እየወሰደ መሆኑንም ገልጸዋል። እንደ አቶ ሰሚር ገለጻ፤ በተለይ ከአካባቢ ብክለት ጋር በተያያዘ በደረቅ ቆሻሻና ፍሳሽ አወጋገድ ጋር ተግባራዊ ያላደረጉ ሁለት ተቋማትን በህግ አግባብነት የመጠየቅ ስራዎች መከናወናቸውን አስረድተዋል። በክልሉ ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ እስከ መስከረም ድረስ ተግባራዊ የሚሆን የአካባቢ ጥበቃ ንቅናቄ እንደሚካሄድም ገልጸዋል። “ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ” በሚል መሪ ሃሳብ የሚከናወነው ይኸው ንቅናቄ የአካባቢ ጥበቃ ውጤታማነትን ለማሳደግ፣ የወጡ ሕጎችና ደንቦች ተግባራዊ እንዲሆኑ፣ በዘርፉ የባለድርሻ አካላትንና የማኅበረሰቡን ሚና ለማጠናከር ያለመ መሆኑን አቶ ሰሚር ተናግረዋል።   በተመሳሳይ የድሬዳዋ አስተዳደር የአካባቢ፣ የደንና የአየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን ስራ አስኪያጅ አቶ አብዱ መሐመድ በበኩላቸው፤ አካባቢን ውብና ፅዱ የስራና የመኖሪያ ስፍራ ለማድረግ የተጀመረውን አገር አቀፍ ዘመቻ ከግብ ለማድረስ በአስተዳደሩ የተቀናጀ ርብርብ እንደሚደረግ ገልጸዋል። አቶ አብዱ እንደሚናገሩት፤ አሁን የምንኖርባት አካባቢ ያለፈው ትውልድ ያወረሰን ብቻ ሳይሆን ከመጪው ትውልድ የተበደርን መሆኑን በመገንዘብ አካባቢን መንከባከብ ያስፈልጋል። ደረቅ ቆሻሻ በተለይም የፕላስቲክ ውጤቶች በመቅበርም ሆነ በማቃጠል አካባቢን ጽዱ ማድረግ እንደማይቻል የገለጹት አቶ አብዱ፤ ፕላስቲኮቹን በጥንቃቄ በመሰብሰብና በመፍጨት ሌሎች ቁሶችን በማምረት እንደሆነ ተናግረዋል። በዚህም በድሬዳዋ አስተዳደር የአካባቢ ብክለትን ለመከላከልና የተፈጥሮ ሀብትን ለመጠበቅ የሚያግዝ የስድስት ወራት ዘመቻ መካሄድ መጀመሩን ገልጸዋል። እስከ መስከረም 30 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ በሚካሄደው በዚሁ ዘመቻ የሚያዝያ በሙሉ የፕላስቲክ ብክለትን በመከላከልና የፕላስቲክ አጠቃቀምን በማዘመን የስነ ምህዳርን ለመጠበቅ የሚያግዙ ህዝባዊ ንቅናቄዎች እንደሚካሄዱ አመልክተዋል። ዘመቻው በተለይ በትምህርት ቤቶች የአካባቢ ጥበቃ ክበቦችንና ሚዲያን በመጠቀም እና በየደረጃው የሚገኘውን ህብረተሰብ ግንዛቤ በማስፋት ድሬዳዋ ለስራና ለኑሮ የምትመች ፅዱና ውብ ለማድረግ የተጀመሩ ጥረቶችን ለማሳካት እንደሚሰራ ነው የተናገሩት ። በተጨማሪም ከከፍተኛ አመራሩ እስከ ህፃናት ተማሪዎች ድረስ የሚሳተፉበት የፕላስቲክ ኮዳዎችን የመሰብሰብ ና ፕላስቲኮችን ወደ ሌላ ምርቶች ለሚለወጡ ድርጅቶች የማስረከብ ስራ ይካሄዳል ብለዋል።  
በአማራ ክልል የፕላስቲክ  አወጋገድን በማዘመን ከብክለት ነፃ  የሆኑ ከተሞችን ለመገንባት ጥረት እየተደረገ ነው
Apr 19, 2024 133
ባህር ዳር ፤ ሚያዚያ 11 / 2016 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል የፕላስቲክና የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ስርዓትን በማዘመን ከብክለት ነፃ የሆኑ ከተሞችን ለመገንባት ጥረት እየተደረገ መሆኑን የክልሉ የአካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አሕመድ በቅርቡ ባስተላለፉት መልዕክት፤ የፕላስቲክ እና የቆሻሻ ብክለት ሥነ ምኅዳራችንን እና ጤናችንን አደጋ ላይ እንደሚጥል መግለጻቸው ይታወሳል። እርሳቸው "በኃላፊነት ስሜት ቆሻሻን በአግባቡ በማስወገድ እና ዘላቂ አማራጮችን በመምረጥ ተፈጥሮን ለትውልድ ማቆየት እንችላለን" በማለት ከተሞችን እና አካባቢያን ጽዱ ለማድረግ የመተባበር አስፈላጊነትን አጽንኦት ሰጥተውታል። የፕላስቲክ ቆሻሻ ለዓመታት ከምድር ላይ የማይጠፋ ለአካባቢ ብክለት ዋነኛ መንስኤ እየሆነ መምጣቱን መረጃዎች ያሳያሉ። በተለይ ከተሞች ለዚህ ችግር ሰለባ ናቸው። በገጠር አካባቢ ለግብርና ስራ ችግር ፈጣሪ እየሆነ መምጣቱና ፕላስቲክ የበሉ ላሞች እንደሚሞቱ ይገለጻል። ይህን እንዴት እየተከላከሉ እንደሆኑ ኢዜአ የጠየቃቸው በአማራ ክልል የአካባቢና ደን ጥበቃ ባለስልጣን የአካባቢና የአየር ንብረት ለውጥ ዳይሬክተር አቶ አወቀ ይቴ በሰጡት ምላሽ "ከፕላስቲክና ከደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ጋር ተያይዞ ሊያጋጥም የሚችለውን ብክለት ለማስቀረት በትኩረት እየተሰራ ነው" ብለዋል። ለዚህም የፕላስቲክና የደረቅ ቆሻሻ አወጋገድ ስርዓትን በማዘመን ከተቋማትና ከሌሎች አካላት ጋር አስተሳስሮ ለመምራት ጥረት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የተለያዩ ማህበራትን በባህር ዳር፣ ደሴ፣ ጎንደርና ሌሎች ትላልቅ ከተሞች በማቋቋም ፕላስቲክን ለይተው በማሰባሰብ የማስወገድ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል። በዚህም በወር ከ30 እስከ 40 ቶን የወዳደቁ ፕላስቲኮች እንደሚሰበሰቡ አመልከተው፤ ከእነዚህም የፕላስቲክ ወንበሮች፣ ለገመድና ሌሎች ምርቶችን በማምረት ጥቅም ላይ እንዲውል እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል። የቀረውንም በመጨፍለቅና በመፍጨት አዲስ አበባን ጨምሮ ወደ ተለያዩ አካባቢዎች የሚጓጓዝበት ሁኔታ እንዳለም ጠቁመዋል። የፕላስቲክ ምርቶች ቀደም ሲል በዘፈቀደ በየቦታው የሚጣልበት ሁኔታ እንደነበረ አስታውሰው፤ "አሁን ላይ የሚጣሉ የፕላስቲክ ቆሻሻዎችን በመሰብሰብና በማስረከብ በርካታ ወጣቶች የገቢ ምንጭ እያደረጉት ይገኛሉ" ብለዋል። ፕላስቲኮች በወንዞንች፣ በውሃ ማፋሰሻ ቦዮችና አካባቢ ስነ-ምህዳር ላይ ጉዳትና ብክለት እንዳያስከትሉ በአሰባሰብና አወጋገዱ ላይ ያተኮረ ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
የአካባቢ ብክለትን መከላከል የሁላችንም ኃላፊነት ሊሆን ይገባል- ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ መሁመድ
Apr 19, 2024 153
ጅግጅጋ፤ ሚያዚያ 11/2016(ኢዜአ)፡- የአካባቢ ብክለትን በመከላከል ፅዱና ለኑሮ የሚመች አካባቢ መፍጠር የሁላችንም ኃላፊነት ሊሆን ይገባል ሲሉ የሶማሌ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሙስጠፌ መሁመድ ገለጹ። ርዕስ መስተዳድሩ የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል በሚቀጥሉት ስድስት ወራት የሚተገበር የህዝብ ንቅናቄ ዛሬ በክልል ደረጃ አስጀምረዋል። በርዕሰ መስተዳድሩ ጽህፈት ቤት በተጀመረው የንቅናቄ መድረክ ርዕሰ መስተዳድር ሙስጠፌ ሙሁመድ እንደተናገሩት በክልሉ የአካባቢ ብክለት ችግር ለመፍታት አንዱ የፕላስቲክ አጠቃቀምና አወጋገድን ማዘመን ያስፈልጋል። በክልሉ እየተስፋፉ ያሉ ከተሞች ላይ በመመስረት አካባቢ ከብክለት ነፃ እንዲሆን ሴክተር መስሪያ ቤቶች በዕቅዳቸው ውስጥ በማካተት እንዲሰሩ ትኩረት እንደሚደረግ ገልጸዋል።   በአርብቶ አደር አካባቢ የቤት እንስሳት በፕላስቲክ አወጋገድ ችግር ጉዳት ይደርስባቸዋል ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ የፕላስቲክ ምርቶችን መልሶ ጥቅም ላይ ለማዋልና በዚህም የስራ እድል ለመፍጠር ሊሰራ እንደሚገባ አሳሰበዋል። የንቅናቄ መድረኩ ህብረተሰቡ በጉዳዮ ዙሪያ በቂ ግንዛቤ ኖሮት የድርሻውን እንዲወጣ ለማነሳሳት መሆኑን አመልክተዋል። የክልሉ የአካባቢ ጥበቃና ገጠር መሬት አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ ኢንጀነር ሙህየዲን አብዲ ፤ የአካባቢ ብክለት በአካባቢ ጤና ላይ ከፍተኛ ጉዳት የሚያስከትል መሆኑን ተናግረዋል። ችግሩን ለመፍታት የህብረተሰቡን ግንዛቤ ለማስፋት ትኩረት ተስጥቶ እንደሚሰራ ገልጸዋል። በንቅናቄው መድረክ የተገኙት የፌደራል የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ንጉሴ ለማ በበኩላቸው፤ በአገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረው ንቅናቄ የአካባቢ ብክለት በሰው እና በእንስሳት ላይ ሊያደረስ የሚችለውን ጉዳት ለማስቀረት ያለመ መሆኑን ገልጸዋል። ባለስልጣን መስሪያ ቤቱ የፕላስቲክ አጠቃቀም ገደብ ላይ ህግ በማዘጋጀት ለሚመለከተው አካል ማቅረቡንም ጠቅሰዋል። "ብክለት ይብቃ! ውበት ይንቃ" በሚል መሪ ሀሳብ የተጀመረው ንቅናቄ በሚቀጥሉት ስድስት ወራት የሚተገበር ስራ እንደሚከናወን ተመልከቷል።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ በመዲናዋ የብክለት መከላከል ንቅናቄን አስጀመሩ
Apr 19, 2024 68
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በመዲናዋ የብክለት መከላከል ንቅናቄን በዛሬው ዕለት አስጀምረዋል። ከንቲባዋ በማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ባሰፈሩት መልዕክት ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ በሚል መሪ ሃሳብ በከተማችን የብክለት መከላከል ንቅናቄ አስጀምረናል ብለዋል። ተፈጥሮ ለአዲስ አበባ የለገሳትን ውበት ያመናመነውን አሰራር ለመቀየር እና የከተማውን ስርዓተ-ምህዳር ለማሻሻል የሚረዱ ሜጋ ፕሮጀክቶች በከፍተኛ ርብርብ፣ በልዩ የአመራር ትኩረት እና በአጠረ ጊዜ መፈጸማቸውን ገልጸዋል።   ከንቲባ አዳነች አቤቤ ፤ ከፍተኛ ለውጥ እያመጡ ካሉት ፕሮጀክቶች መካከል ዋነኞቹ ለሞቱት የከተማዋ ወንዞች ትንሳኤያቸውን፤ ለተበከሉት ደግሞ ህክምናን ያበሰረው የአዲስ አበባ ወንዞች ዳርቻ ልማት አንዱና መሰረታዊ መሆኑን ጠቅሰዋል። በከፍተኛ ፍጥነት እየቀነሰ የነበረውን የከተማዋን የአረንጓዴ ሽፋን የታደገው እና ከነበረበት 2 ነጥብ 8 በመቶ ወደ 15 በመቶ ያሳደገው የአረንጓዴ አሻራ ማኖር ኢኒሼቲቭ ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸዋል። የተሰሩት ስራዎች አዲስ አበባን የቱሪስት መዳረሻና ዓለም አቀፍ የስበት ማዕከል ያደረጓት ቢሆንም፤ አሁንም ድረስ የድምጽ እና የፍሳሽ ብክለት እና አወጋገድ የከተማዋ ፈተናዎች ሆነው መቀጠላቸውን ተናግረዋል። በሕግና በአሰራር ችግሩን ለመፍታት ከሚደረግ ጥረት ባሻገር፤ ለሚቀጥሉት ስድስት ወራት የሚቆይ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች በመስራት ለውጥ ለማምጣት ንቅናቄው በዛሬው ዕለት በይፋ መጀመሩን አስታውቀዋል።
በክልሉ የአካባቢ ብክለትን በመከላከልና በመቆጣጠር  ሂደት ህዝቡ ጠንካራ ተሳትፎ ሊያደርግ ይገባል..ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ
Apr 18, 2024 378
አርባ ምንጭ፤ ሚያዚያ 10/2016(ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የአካባቢ ብክለትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በሚደረገው እንቅስቃሴ ህዝቡ ጠንካራ ተሳትፎ እንዲያደርግ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ አሳሰቡ። “ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ” በሚል መሪ ሃሳብ ክልል አቀፍ የብክለት መከላከል ንቅናቄ ዛሬ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሂዷል። የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ እንደገለጹት፤የአካባቢ ብክለትን መቆጣጠር አለመቻል ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር ይዳርጋል። የሰውና የእንስሳት ህልውናን አደጋ ላይ ከመጣሉም በላይ በቱሪስት ፍሰትና ኢንቨስትመንት ልማት ላይ አሉታዊ ተጽእኖ እንደሚያስከትል አመልክተዋል ። በተለይ ኢንዱስትሪዎች እና ሌሎች አገልግሎት ሰጭ ተቋማት የሚያስከትሉትን የአካባቢ ብክለት ለመከላከል የመፍትሄ ሀሳቦችን የማቅረብ ብሎም ተቋማቱን መከታተልና መቆጣጠር ያስፈልጋል ብለዋል። በዚህ ረገድ የክልሉ መንግሥት አካባቢን ከብክለት ለማዳን መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ የሃይማኖት አባቶችና የአገር ሽማግሌዎችን በማሳተፍ እየሠራ መሆኑን አመልክተዋል። ህብረተሰቡ በተለይም የፕላስቲክ ቁሳቁሶችን በአግባቡ በመጠቀምና በማስወገድ እንዲሁም የአየር፣ የውሃና የአፈር ሀብቶችን ከብክለት በመጠበቅ ድርሻውን እንዲወጣ አሳስበዋል።   የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ደን፣ አካባቢ ጥበቃና ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ግዛቴ ግጄ በበኩላቸው፤ በአካባቢ ብክለት ሳቢያ በሚመጡ የሙቀት መጠን መጨመር፣ የበሽታ ክስተት፣ በረሃማነት መስፋፋት፣ ምርትና ምርታማነት መቀነስ የህዝብ የመኖር ህልውና አደጋ ላይ የሚጥል መሆኑን ተናግረዋል ። "ከተፈጥሮ ጋር ሳንስማማ መኖር አንችልም" ያሉት ሃላፊው፤ ህዝቡ የችግሩን አሳሳቢነት በመረዳት አካባቢውን ከብክለት መጠበቅ እንደሚገባ አመልክተዋል። "ዛሬ በይፋ የተጀመረው ክልል አቀፍ የአካባቢ ብክለት መከላከል ዘመቻ ለስድስት ወራት ይቆያል" ብለዋል። የአካባቢ ብክለትን በመደበኛ ስራ ብቻ መከላከል የማይቻል መሆኑን ጠቁመው፤ የተለያዩ ተቋማት፣ ህዝብና መንግስት በቅንጅት እንዲሠሩ በማስቻል ቆሻሻን በአግባቡ በማስወገድ ንቅናቄውን ማሳካት ይገባል ብለዋል።   ኢትዮጵያ በአረንጓዴ ልማት ያስመዘገበችውን ድል በአካባቢ ብክለት መከላከል መድገም ይገባል ያሉት ደግሞ የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬነሽ መኩሪያ ናቸው ። በአሁኑ ወቅት ባለስልጣኑ የበኩሉን እየተወጣ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ ዜጎች የአካባቢ ብክለትን በመከላከል የፀዳችና የለማች ኢትዮጵያን ለትውልድ ለማውረስ የሚደረገውን ጥረት በተቀናጀ መንገድ መደገፍ እንደሚገባቸው አመልክተዋል። ቆሻሻን በአግባቡ መጠቀምና ማስወገድ ባለመቻሉ በሰውና እንስሳት ጤና ላይ ጉዳት ከማስከተልም በላይ ለስርዓተ ምህዳር መዛባትና ለብዝሃ ህይወት የመጥፋት ምክንያት በመሆኑ መከላከል ይገባናል ብለዋል። የፕላስቲክ ምርቶች ሳይበሰብሱ ለብዙ ዘመናት የሚቆዩ በመሆናቸው ህብረተሰቡ ከፕላስቲክ ምርት ይልቅ ባህላዊና አገር በቀል ቁሳቁሶችን መጠቀም እንደሚገባውም ወይዘሮ ፍሬነሽ ተናግረዋል። በንቅናቄ መድረኩ በክልሉ የሚገኙ 10 ዞኖች በቀጣይ ተራራን እንዲያለሙ የተራራ ልማት ካርታ ርክክብ ተደርጓል፡፡    
በኢትዮጵያ ለአካባቢ ተስማሚ የኢንዱስትሪ ስርዓትን በመገንባት ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል-ኢንስቲትዩቱ
Apr 18, 2024 149
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2016(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ለአካባቢ ምቹና ተስማሚ የኢንዱስትሪ ስርዓትን በመገንባት በዘርፉ ቀጣይነትና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የአምራች ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ የጨርቃጨርቅና አልባሳት ኢንዱስትሪዎች ከአካባቢ ጋር ተስማሚ በሆነ መንገድ ዘላቂና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ የሚያግዝ ፕሮጀክት ዛሬ ይፋ አድርጓል። የኢንስቲትዩቱ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ስለሺ ለማ ፕሮጀክቱ በጨርቃጨርቅና አልባሳት ዘርፍ የሚደረጉ የምርት እንቅስቃሴዎች አካባቢን በማይጎዳ መልኩ እንዲከናወኑ የሚያግዝ እንደሆነ ገልጸዋል። በመንግስትና በልማት አጋር ድርጅቶች የተቀረጸው ይህ ፕሮጀክት አምራቾች በዘላቂነት በአገር ውስጥና በውጭ ተወዳዳሪ ሆነው ምርታቸውን እንዲያቀርቡ የሚያበረታታ ስለመሆኑም ጠቅሰዋል። አምራቾች የምርት ሂደታቸው በአካባቢ ላይ ተጽእኖ እንዳያደርስ የተረፈ ምርት አጠቃቀምና የኬሚካል አስተዳደርና አያያዝ ላይ ያላቸውን አቅም ለማሳደግ ይርዳል ብለዋል። ለአምስት ዓመታት በሚተገበረው ፕሮጀክት በጨርቃጨርቅ አምራች ኢንዱስትሪዎች ለምርት ጥቅም የሚውሉ ኬሚካልና ፍሳሾችን በማጣራት መልሰው ጥቅም ላይ የሚውሉበት አሰራር መኖሩንም አክለዋል። በኢንዱስትሪ ፓርኮች የጋራ የፍሳሽ ማጣሪያን በመገንባት እየተሰራ ሲሆን፥ ይህም ዘላቂነት ያለውና ከአካባቢ ጋር የተስማማ ኢንዱስትሪን እውን ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን አንስተዋል። እንደ ምክትል ዋና ዳሬክተሩ ገለጻ የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ኢንዱስትሪ በውጪ ንግድ፣ በስራ እድል ፈጠራ፣ ከውጭ የሚገቡ ምርቶችን በመተካት ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ይገኛል።   የተባበሩት መንግስታት የኢንዱስትሪ ልማት ድርጅት የኢትዮጵያ ተወካይና ዳሬክተር ካላብሮ አውሬሊያ በተወካያቸው ጽጋቡ ተካ በኩል ባስተላለፉት መልዕክት ድርጅቱ ለኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ልማት ትብብር እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል። የጨርቃ ጨርቅና አልባሳት ኢንዱስትሪዎች ከአካባቢ ጋር ተስማሚ በሆነ መንገድ ዘላቂና ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ይፋ ለተደረገው ፕሮጀክት መሳካትም የልማት አጋርነታቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል።                            
በአዲስ አበባ ለስድስት ወራት የሚቆይ የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄ  ሊካሄድ ነው
Apr 18, 2024 150
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 10/2016(ኢዜአ)፡-በአዲስ አበባ ለስድስት ወራት የሚቆይ የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄ የሚካሄድ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ስራ አስኪያጅ ድዳ ድሪባ፤ በሰጡት መግለጫ ከተማ አቀፉ የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄ "ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ" በመሪ ሃሳብ ይካሄዳል ብለዋል። የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄው ከነገ ሚያዚያ 11 ቀን 2016 እስከ መስከረም 2017 ዓ.ም የሚካሄድ መሆኑንም ተናግረዋል። የመረሃ ግብሩ ማስጀመሪያም በነገው እለት በአድዋ ድል መታሰቢያ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሃላፊዎች፣ የሐይማኖት አባቶች፣ የህብረተሰብ ተወካዮችና ሌሎችም እንግዶች በተገኙበት በይፋ የሚጀመር መሆኑን ጠቁመዋል። ለስድስት ወራት በሚዘልቀው የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄ መረሃ ግብር ህብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ የተለያዩ ብክለቶችን የመከላከልና ግንዛቤ የመፍጠር ተግባራት ይከናወናሉ ብለዋል። በመርሃ ግብሩ መሰረት በሚያዚያ ወር በዋነኝነት የፕላስቲክ ብክለትን ለመከላከል በየቦታው የተጣሉ ፕላስቲኮችን የማስወገድ ስራ ሲከናወን በግንቦት ደግሞ የአየር ብክለትን መከላከል ላይ ይተኮራል ነው ያሉት። በመቀጠልም በሰኔ የውሀ ብክለትን ለመከላከል ወንዞችን የማጽዳት፣ በሃምሌ የአፈር ብክለትን፣ በነሃሴ የድምፅ ብክለትን የመከላከል ስራዎች የሚከናወኑ መሆኑ ተመላክቷል። በመጨረሻም በመስከረም ወር በማህበራዊ ዘርፍ የሚከናወኑ ስራዎች የሚያደርሱትን ተጽእኖ በመገምገም የንቅናቄ መርሃ ግብሩ የሚጠናቀቅ መሆኑ ታውቋል።
የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አቀፍ የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄ መድረክ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ነው
Apr 18, 2024 145
አርባ ምንጭ፤ ሚያዝያ 10/2016(ኢዜአ)፦የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አቀፍ የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄ መድረክ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ነው። የአካባቢ ብክለት መከላከል ንቅናቄው "ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ" በሚል መሪ ሀሳብ ለስድስት ወራት እንደሚካሄድ ታውቋል። ንቅናቄው በክልሉ የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል የሚከናወኑ ተግባራትን በማህበረሰብ ተሳትፎ ከግብ ለማድረስ ያለመ መሆኑም ተገልጿል። በአርባ ምንጭ ከተማ ንቅናቄውን ለማስጀመር በተዘጋጀ መድረክ ላይ በፕላስቲክ ብክለት፣ በደን ጭፍጨፋ እና በቀጣይ የሥራ አቅጣጫዎች ላይ ያተኮሩ ሰነዶች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል። በንቅናቄ መድረኩ ላይ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ፣ የኢፌዴሪ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬነሽ መኩሪያ፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፀሐይ ወራሳ፣ የክልሉ ደን፣ አካባቢ ጥበቃና ልማት ቢሮ ሃላፊ አቶ ግዛተ ግጄን ጨምሮ በየደረጃው ያሉ የሥራ ሃላፊዎች ተገኝተዋል።  
ባለፉት ዘጠኝ ወራት የአካባቢ ብክለት ተጽእኖ ባደረሱ 1 ሺ 720 ተቋማት ላይ  እርምጃ ተወስዷል-ባለስልጣኑ
Apr 18, 2024 153
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 10/2016(ኢዜአ)፦ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የአካባቢ ብክለት ተጽእኖ ባደረሱ 1 ሺ 720 ተቋማት ላይ እርምጃ መውሰዱን የአዲስ አበባ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን አስታወቀ፡፡ የባለስልጣኑ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ድዳ ድሪባ ለኢዜአ እንዳሉት ባለስልጣኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በርካታ የቁጥጥር ስራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል፡፡ በዚህም በዘጠኝ ወራት 7 ሺ 294 ተቋማትን ለመቆጣጠር አቅዶ 7 ሺ 598 ተቋማትን በመቆጣጠር ከዕቅዱ በላይ ማሳካቱን ተናግረዋል፡፡ በተደረገው ጥብቅ ቁጥጥርና ክትትል በአካባቢ ላይ ብክለት ባደረሱ 1 ሺ 720 ተቋማት ላይ እርምጃ መወሰዱን አረጋግጠዋል፡፡ ከተቋማቱ መካከል 1 ሺ 661ዱ ማስጠንቀቂያ የተሰጣቸው ሲሆን በተቀመጠላቸው አቅጣጫ መሰረት ተግባራቸውን ሳያከናዉኑ የቀሩ 59 ተቋማት መታሸጋቸውን ተናግረዋል፡፡ ባለስልጣኑ የአካባቢ ተጽእኖን ለመቆጣጠር በተሰጠው ተልዕኮ መሰረት ተቋማት ህጎችን አክብረው እንዲሰሩ የጀመረውን ቁጥጥርና ክትትል አጠናክሮ መቀጠሉን አብራርተዋል፡፡    
በኦሮሚያ ክልል ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ የሚሰጡ ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ መሆኑ ተገለጸ
Apr 15, 2024 619
አዳማ ፤ ሚያዚያ 7/2016(ኢዜአ)፡- በኦሮሚያ ክልል በመጪው ክረምት የሚተከሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞች ዝግጅት በስፋት እየተከናወነ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ ግብርና ቢሮ የደን ልማትና እንክብካቤ ዘርፍ ዳይሬክተር አቶ ከተማ አብዲሳ ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክልሉ ከጥር 1 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ወራት የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ፣ የእርከን ማሰርና የተራቆቱ መሬቶችን ከንኪኪ ነፃ የማድረግ ስራ ተከናውኗል። በዚህ ረገድ በምስራቅና ምዕራብ ሐረርጌ ዞኖች የተከናወነው የተፋሰስና እርከን ማሰር ስራ ለሌሎች የክልሉ ዞኖች ጭምር ተሞክሮ እንደሚሆን ተናግረዋል። በአብዛኛው የተፋሰስ ልማት ስራ በተከናወነባቸው መሬቶች ላይ የሚተከሉ ችግኞችን በስፋት የማዘጋጀት ተግባርም ጎን ለጎን እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። በክልሉ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ የሚሰጡ ችግኞችን የማዘጋጀት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው የእስካሁኑ አፈጻጸምም የተሻለ መሆኑን አብራርተዋል። የፍራፍሬ ችግኞች፣ ቀርከሃና ለጥምር ደን አገልግሎት የሚውሉ ችግኞች ትልቅ ትኩረት ማግኘታቸውን አመልክተዋል። ከተዘጋጁት ችግኞች ውስጥ 40 በመቶ ለደን አገልግሎት የሚውልና 10 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ የፍራፍሬ ችግኞች መሆናቸውን የገለፁት አቶ ከተማ ፤ ለተከላ የበቁ ችግኞችን የመለየት ስራ እየተከናወነ መሆኑንም ተናግረዋል። የችግኝ መትከያ ጉድጓድ የማዘጋጀት ስራም እየተከናወነ ሲሆን በክልሉ 1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ችግኝ ለመትከል መታቀዱንም ተናግረዋል። በዚህም ከ800 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነውን መሬት የመለየት ስራ መከናወኑን ጠቅሰዋል። የምስራቅ ሸዋ ዞን ግብርና ጽሕፈት ቤት ምክትል ሃላፊ አቶ አብነት ዘገየ በበኩላቸው ፤በዞኑ ዘንድሮ የሚተከል 279 ሚሊዮን የተለያየ አገልግሎት ያላቸው ችግኞች የማዘጋጀት ስራ እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። በዞኑ 13 ወረዳዎች በተለዩ ከ300 በላይ ተፋሰሶች ላይ ለ60 ቀናት የአፈርና ውሃ እቀባ ስራ መከናወኑ አስታውሰው፤ በመጪው ክረምት የፍራፍሬ ጨምሮ ሌሎችንም ችግኞች ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝ አስረድተዋል። በተለይ ሀገር በቀል ዛፎች፣ የፍራፍሬ፣ ቀርከሃና ቴምርን ጨምሮ ለእንስሳት መኖ የሚውሉትን ለመትከል ከተፋሰስ ስራው ጎን ለጎን የጉድጓድ ዝግጁቱ አሁንም ተጠናክሮ መቀጠሉን አመልክተዋል።      
ምቹ የመኖሪያና የሥራ አካባቢ በመፍጠር ሁሉን አቀፍ ልማት ለማሳካት የተቀናጀ ርብርብ ሊደረግ እንደሚገባ ተመላከተ
Apr 13, 2024 862
ድሬዳዋ፤ ሚያዝያ 5/2016(ኢዜአ)፦ ለዜጎች ምቹ የመኖሪያና የሥራ አካባቢ በመፍጠር የተጀመረውን ሁሉን አቀፍ ልማት ለማሳካት የተቀናጀ ርብርብ እንዲደረግ የኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን አስገነዘበ። በድሬዳዋ ከተማ "የፕላስቲክ አጠቃቀም ዘይቢያችንን እናዘምን" በሚል መሪ ሃሳብ የንቅናቄ መድረክ ዛሬ በይፋ ተጀምሯል። በመድረኩ "ብክለት ይብቃ፤ ውበት ይንቃ" በሚል መሪ ሃሳብ የተዘጋጀ ሲሆን፤ በድሬዳዋ አስተዳደር ደረጃ የሚካሄደው የአካባቢ ብክለት የመከላከል ንቅናቄ አካል ነው። የኢትዮጵያ አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ፍሬነሽ መኩሪያ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት ንቅናቄው አካባቢን እየጎዳ ያለውን የፕላስቲክ ቆሻሻ ብክለትን ለመቀነስ ያለመ ነው። የፕላስቲክ ብክለት በሰውና በእንሰሳት ጤና ላይ ከፍተኛ ችግር እያደረሰ መሆኑንም ገልጸዋል። ከአነስተኛ እስከ ዋና ዋና ከተሞቻችን በፕላስቲክ ቆሻሻ የተጥለቀለቁ፣ የኑሮና የስራ ሂደቶችን እያደናቀፉ ለብዝሃ ህይወት መመናመን ምክንያት እየሆኑ ይገኛሉ ብለዋል። በመሆኑም ይህንን በማህበራዊና የምጣኔ ሃብት እንቅስቃሴዎች ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖ የሚፈጥረውን ችግር በተቀናጀ ህዝባዊ ንቅናቄ በመታገዝ መፍትሄ ለማምጣት ርብርብ እንዲደረግ አሳስበዋል። በተለይም ችግሩን ለመቀነስ የተዘጋጁ ስትራቴጂ፣ የህግ ማዕቀፎችና የማስፈፀሚያ ስልቶችን በተቀናጀ መንገድ በመተግበር ዘላቂ የአካባቢ አጠቃቀም ለመፍጠር መሥራት እንደሚያስፈልግም አብራርተዋል። በተጨማሪም በአየር ንብረት ለውጥ ምክንያት የሚደርሰውን የደን መራቆትና የተፈጥሮ ሃብት መመናመን ችግር ለመታደግ የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን መተግበር ይገባል ብለዋል። ባለሥልጣኑ በአስተዳደሩ ለተጀመረው ህዝባዊ ንቅናቄ ስኬት ድጋፍ እንደሚያደርግም ወይዘሮ ፍሬነሽ አረጋግጠዋል።   የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ አቶ ሀርቢ ቡህ በበኩላቸው በንቅናቄው የአካባቢ ፖሊሲና የህግ ማዕቀፎች በተቀናጀ መንገድ በመተግበር ምቹ የሥራ፣ የመኖሪያ እና የኢንቨስትመንት መዳረሻ ከተማ ለመፍጠር እንደሚሰራ ተናግረዋል። የተጀመረው ንቅናቄ በሚቀጥሉት ስድስት ወራት በአስተዳደሩ በፕላስቲክ፣ በአየር፣ በውሃ፣ በአፈር፣ በድምፅ ብክለቶች ላይ ሰፋፊ ስራዎች እንደሚከናወኑ ገልጸዋል።   በንቅናቄው ላይ ለ5ሺህ ነዋሪዎችና ባለድርሻ አካላት ግንዛቤ በመፍጠርና የፕላስቲክ ውጤቶችን መልሶ መጠቀም የሚያስችሉ ስራዎች ውጤታማ እንዲሆኑ እንደግፋለን ያሉት ደግሞ የድሬዳዋ የአካባቢ፣ የደንና የአየር ንብረት ለውጥ ባለስልጣን ስራ አስኪያጅ አቶ አብዱ መሐመድ ናቸው።
የብሔራዊ ዘላቂ ኢነርጂ ልማት ስትራቴጂ ወጥ የኢነርጂ አሰራር ስርአት ለመፍጠር ወሳኝ ነው - የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር
Apr 12, 2024 690
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 4/2016(ኢዜአ)፦የብሔራዊ ዘላቂ ኢነርጂ ልማት ስትራቴጂ ወጥ የኢነርጂ አሰራር ስርአት ለመፍጠርና የኢነርጂ ሃብትን በአግባቡ ለመጠቀም ወሳኝ መሆኑን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር ገለጸ። የኢነርጂ ልማት ስራ ወጥነት ባለው መልኩ እንዲተገበርና የኢነርጂ ተደራሽነትን ለማስፋት ስትራቴጂው ወሳኝ ሚና እንዳለው ተገልጿል። የብሔራዊ ዘላቂ ኢነርጂ ልማት ስትራቴጂ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በዛሬው እለት ይፋ የተደረገ ሲሆን ስትራቴጂውን የተመለከተ አውደ ጥናትም ተካሄዷል።   የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኢነርጂ ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ፤ በስትራቴጂ የታገዘ ዘላቂ የኢነርጂ አጠቃቀምን መከተል አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። የኃይል ምንጮችን መጠቀም ለዘላቂ የኢነርጂ ልማት እውን መሆን ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው ለዘርፉ ስራ ከፍተኛ የኢንቨስትመንት ያስፈልጋል ብለዋል። በመሆኑም በዘርፉ ያሉ እድሎችንና አማራጮችን ከግምት ውስጥ በማስገባት የብሔራዊ ዘላቂ ኢነርጂ ልማት ስትራቴጂ መዘጋጀቱን ተናግረዋል። ከውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎትና የነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣን የተወጣጣ የባለሙያዎች ቡድን ስትራቴጂውን ለማዘጋጀት 1 ዓመት ከ6 ወር ጊዜ የወሰደ መሆኑንም ጠቅሰዋል። የኢነርጂ ፖሊሲ መሬት ወርዶ በሚፈለገው ደረጃ እንዲተገበር፣ የኢነርጂ ሀብቶችን በተመለከተ የተቀናጀ መረጃ ለመስጠትና የግሉ ዘርፍ ያለውን ድርሻ ለማሳደግ ስትራቴጂው የላቀ ጠቀሜታ ይኖረዋል ብለዋል። በተበታተነ መልኩ ይተገበር የነበረውን የኢነርጂ የአሰራር ማዕቀፍ ወጥነት እንዲኖረው የሚያስችል መሆኑንም ገልጸዋል። ከዚህ በፊት ስትራቴጂውን የተመለከቱ ስድስት የግብአት ማሰባሰቢያ መድረኮች መካሄዳቸውን አስታውሰው የአሁኑ የመጨረሻ ነው ሲሉ ተናግረዋል። የስትራቴጂው የማጠናቀቂያ ስራዎች ከተከናወኑ በኋላም በ2017 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ ወደ ትግበራ ይገባል ብለዋል።   በኢትዮጵያ የጀርመን ኤምባሲ የኢኮኖሚ ዘርፍ ኃላፊ ሬቤካ አልት፤ የሀገራቸው መንግስት በጀርመን ዓለም አቀፍ የልማት ትብብር ድርጅት (ጂ አይ ዜድ) በኩል ለስትራቴጂው ዝግጅት ድጋፍ ማድረጉን አመልክተዋል። ለስትራቴጂው መዳበር አውደ ጥናቶች እንዲካሄዱ ማድረግና የአቅም ግንባታ ስራዎችን ጨምሮ የተለያዩ የቴክኒክ ድጋፎችን ማድረጉን አስታውሰዋል። ጀርመን በኢነርጂው ዘርፍ ለኢትዮጵያ የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ የምትቀጥል መሆኑንም ተናግረዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የውሃና ኢነርጂ ልማት ቢሮ የአማራጭ ኢነርጂ ጥናት ልማት ክትትል ዳይሬክተር የሱፍ ሙባረክ ስትራቴጂው የኢነርጂ ሃብትን በአግባቡ ለመጠቀም የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። የሶማሌ ክልል ማዕድን ኢነርጂና ነዳጅ ቢሮ የኢነርጂ ዘርፍ ዳይሬክተር መሐሙድ መሐመድ እና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የማዕድንና ኢነርጂ ልማት ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ገብረማርያም ሰጠኝ ስትራቴጂው ለዘርፉ ልማትና ተጠቃሚነት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ሴቶች የኢነርጂ ማህበር ምክትል ፕሬዝዳንት ሊንዳ ላጲሶ፤ የግሉ ዘርፍ በኢነርጂው ዘርፍ ያለውን ተሳትፎ ለማሳደግ እንዲሁም እውቀትና ቴክኖሎጂን ስራ ለማዋል ስትራቴጂው ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። የብሔራዊ ዘላቂ ኢነርጂ ልማት ስትራቴጂ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጠጣር ከ2024 እስከ 2030 ተግባራዊ እንደሚሆን በአውደ ጥናቱ ላይ ተመላክቷል።          
በሚቀጥሉት ቀናት በአብዛኛው የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ ሥፍራዎች የተሻለ እርጥበት ይኖራቸዋል
Apr 12, 2024 575
አዲስ አበባ ፣ሚያዚያ 04/ 2016 (ኢዜአ)፡-በቀጣይ ስምንት ቀናት ዝናብ ሰጪ የሚቲዎሮሎጂ ገፅታዎች በአብዛኞቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ እየተጠናከሩ እንደሚሄዱ የኢትዮጵያ የሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለፀ። ኢንስቲትዩቱ ለኢዜአ በላከው መግለጫ፤ ዝናብ ሰጪ የሚቲዎሮሎጂ ገፅታዎች፤ በአብዛኞቹ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ የአገሪቱ አካባቢዎች እየተጠናከሩ እንደሚሄዱ አመላክቷል። ከዚሁ ጋር በተያያዘም በደቡብ፣ በደቡብ ምዕራብ፣ በመካከለኛው ምሥራቅና በስምጥ ሸለቆ አካባቢዎች የተሻለ ጥንካሬ እንደሚኖረውም በትንበያው ተገልጿል። በሚቀጥሉት ቀናትም በአብዛኛው የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ ሥፍራዎች የተሻለ እርጥበት እንደሚኖራቸውና የግብርና ሥራዎችን ለማከናወን እንደሚጠቅሙ ገልጿል። ይህም የረዥም ጊዜ ሰብሎችን ለመዝራት፤ በቡቃያና በተለያየ የዕድገት ደረጃ ላይ ለሚገኙ የበልግ ሰብሎችና ለቋሚ ተክሎች የውኃ ፍላጎት መሟላት፤ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ነው የጠቆሙት። የሚጠበቀው እርጥበታማ ሁኔታ ለእርሻ ሥራ እንቅስቃሴ አመቺ ሁኔታን ስለሚፈጥር አርሶ አደሮች ተገቢ የሆኑ ግብዓቶችን በመጠቀም የእርሻ ሥራቸውን በተሟላ መልኩ ማካሄድ እንደሚገባቸው ገልጿል። በሚቀጥሉት ቀናት በኦሞ ጊቤ፣ ስምጥ ሸለቆ፤ በላይኛውና በመካከለኛው ባሮ አኮቦ፤ አዋሽ፣ አባይ፣ ገናሌ ዳዋ፣ በመካከለኛው ተከዜ እና በላይኛው ዋቢ ሸበሌ ተፋሰሶች ከፍተኛ የእርጥበት ሁኔታ እንደሚኖር ጠቁሟል። ከዚህም ጋር ተያይዞ የሚጠበቀው ከፍተኛ እርጥበት፤ ለገፀ ምድርም ሆነ ለከርሰ ምድር ውሃ ኃብት መጎልበት አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው ኢንስቲትዩቱ አስታውቋል።  
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል በህብረተሰብ ተሳትፎ የአካባቢ ብክለትን ለመከላከል በትኩረት ይሰራል
Apr 12, 2024 377
ሚዛን አማን ፤ሚያዚያ 4/2016 (ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የአካባቢ ብክለትን ለመግታት ከኅብረተሰቡ ጋር በቅንጅት እንደሚሠራ የክልሉ ደን፣ አካባቢ ጥበቃና አየር ንብረት ለውጥ ቢሮ አስታወቀ። ቢሮው "ብክለት ይብቃ ውበት ይንቃ" በሚል መሪ ቃል በአካባቢ ጥበቃ ሥራ ላይ ግንዛቤ መፍጠርን ዓላማው ያደረገ መድረክ በቴፒ ከተማ እያካሄደ ነው።   በመድረኩ ላይ የቢሮው ኃላፊ ዶክተር ኢንጂነር አሥራት ገብረማርያም እንዳሉት የአካባቢ ብክለት ከተፈጥሯዊ ይልቅ በሰው ሰራሽ ምክንያት በስፋት ይከሰታል። ለሰው ሰራሽ የአካባቢ ብክለት መስፋት የኅብረተሰቡ የግንዛቤ እጥረት በዋናነት በምክንያትነት እንደሚጠቀስ ገልጸው፣ የህብረተሰቡን ግንዛቤ በትምህርት መቀየር አስፈላጊ በመሆኑ ዛሬ የንቅናቄ ዘመቻ ተጀምሯል ብለዋል። የአካባቢ መበከል ለአየር ጸባይ ለውጥ መንስኤ ከመሆኑ ባለፈ ለቀጣይ ትውልድ ፈተና እንደሚሆንም ተናግረዋል። ለሚቀጥሉት ስድስት ወራት ብክለትን ለመከላከል በንቅናቄ የሚሰራው የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ በሁሉም መዋቅሮች በበካይ ቁሶች እና ድርጊቶች አወጋገድ ላይ ትኩረት ይደረጋል ብለዋል። በክልሉ ጽዱና ለኑሮ ምቹ የሆነ አካባቢን ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት በየደረጃው ያለ አመራርና ኅብረተሰቡ ተግባራዊ ተሳትፎ በማድረግ ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ጠይቀዋል።   በመድረኩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የክልሉ መንግስት ረዳት ተጠሪ አቶ በላይ ተሰማ የአየር ንብረት ለውጥ በሰው ህይወት ላይ የሚያስከትለውን ተጽዕኖ በመገንዘብ ብክለትን መከላከል የሁሉም ድርሻ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል። "መንግስት ከሕዝቡ ጋር ተቀናጅቶ የአየር ንብረት ለውጥ ተጽኖን ለመቋቋም የሚያስችሉ ተግባራትን እያከናወነ ነው" ያሉት አቶ በላይ፣ ለእዚህም የአረንጓዴ አሻራ መርሀግብር ሥራን ለአብነት ጠቅሰዋል። የአካባቢ መበከል የጤና እክል እንደሚያስከትል ገልጸው፣ "አካባቢን ውብና ለመኖር ምቹ ማድረግ ቱሪዝምን በማሳደግ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ስለሚያረጋገጥ ክልሉ በትኩረት ይሠራል" ብለዋል። በቴፒ ከተማ እየተካሄደ ባለው ክልላዊ የንቅናቄ መድረክ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ የዞኖችና የከተማ አስተዳደሮች ባለድርሻ አካላት እየተሳፉ ነው።
በበልግ ዝናብ ምክንያት የከፋ ጉዳት እንዳይደርስ ከክልሎች፣ ከከተሞችና ከወረዳዎች ጋር የተቀናጁ የአደጋ ስጋት ቅነሳ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑ ተገለጸ
Apr 8, 2024 955
ድሬዳዋ ፤ መጋቢት 30/2016(ኢዜአ)፦ እየጣለ የሚገኘው የበልግ ዝናብ በሚያስከትላቸው ጎርፍና ተያያዥ አደጋዎች የከፋ ጉዳት እንዳይደርስ ከክልሎች፣ ከከተሞችና ከወረዳዎች ጋር የተቀናጁ የአደጋ ስጋት ቅነሳ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑ ተገለጸ። የአደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽነር አምባሳደር ዶክተር ሺፈራው ተክለማርያም የተመራ ቡድን በድሬዳዋ አስተዳደር የጎርፍና የአደጋ ስጋትን ለመቀነስና በዘላቂነት ለመቋቋም እየተሰሩ በሚገኙ ተግባራት ዙሪያ ዛሬ ከአስተዳደሩ አመራር አባላት ጋር ተወያይቷል። ኮሚሽነሩ በዚሁ ጊዜ ለኢዜአ እንደተናገሩት እየጣለ የሚገኘው የበልግ ዝናብ በሚያስከትላቸው ጎርፍና ተያያዥ አደጋዎች ሁለት ሚሊዮን የሚሆኑ የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ ማህበረሰብ የአደጋ ስጋት ተጎጂዎች ሊሆኑ ይችላሉ ። እነዚህን የማህበረሰብ ክፍሎች ከአደጋ ስጋት ለመታደግ ከበልግ ዝናብ ተጠቃሚዎች ክልሎች፣ ከተሞችና ወረዳዎች ጋር የተቀናጁ የአደጋ ስጋት ቅነሳ ስራዎች እየተሰሩ ናቸው ብለዋል። ኅብረተሰቡም ራሱን ከአደጋ እንዲከላከል የሚሰጠውን ምክር በአግባቡ ተግባራዊ እንዲያደርግ ኮሚሽነሩ አሳስበዋል። በድሬዳዋ ከተማ በበልግና በክረምት ወቅቶች የሚከሰቱ ጎርፍና ደራሽ የአደጋ ስጋቶች ለመቀነስ የተጀመሩ ሥራዎች በአርአያነት እንደሚጠቀሱ አምባሳደር ሺፈራው አመልክተዋል። በተጨማሪም "ሰብዓዊ ድጋፍ በራስ አቅም" የሚለውን አገር አቀፍ አቅጣጫ ለመተግበር የዘረጋው የሀብት ማሰባሰቢያ መንገድም ለሌሎችም አካባቢዎች በተሞክሮነት የሚወሰድና የሚተገበር ይሆናል ብለዋል። ደራሽና ድንገተኛ የሆኑ የአደጋ ክስተቶችን ለመቋቋምና ለአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር ማህበረሰብ ለመፍጠር የሚደረገው ርብርብ መጠናከር እንዳለበት ያሳሰቡት አምባሳደር ሺፈራው፣ ለዚህም ኮሚሽኑ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ አረጋግጠዋል። የድሬዳዋ አስተዳደር ምክትል ከንቲባና የአደጋ ስጋት አመራር ምክር ቤት ሰብሳቢ ሀርቢ ቡህ፣ በአስተዳደሩ የጎርፍ አደጋን ለመቀነስ በተመደበ ከፍተኛ በጀት በአራት የጎርፍ መውረጃዎች ላይ የተገነቡት የመከላከያ ግንቦች ችግሩን በመቀነስና በመከላከል ስራው መሠረታዊ ውጤት ማስገኘታቸውን ተናግረዋል።   የአስተዳደሩ ግብርና ቢሮም የጎርፍ ውሃን በማቆር ለምርትና ምርታማነት እንዲውል እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። የድሬዳዋን መተባበርና የመረዳዳት ባህልን በመጠቀም ከተማሪ እስከ ባለፀጋዎች የሚሳተፉበት የሀብት ማሰባሰቢያ ሥርዓት ተዘርግቶ ወደ ሥራ መገባቱን ምክትል ከንቲባው አስረድተዋል። በኮሚሽነር ሺፈራው የተመራው ቡድን በአስተዳደሩ የአደጋን መከላከል ሥራዎችን ተዘዋውሮ እንደሚመለከት ተገልጿል።  
በአማራ ክልል የአረንጓዴ አሻራ ልማት መርኃ-ግብር ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል- ዶክተር ድረስ ሳህሉ
Apr 5, 2024 614
ባህር ዳር፤ መጋቢት 27 ቀን 2016 (ኢዜአ)፡-በአማራ ክልል የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በክልሉ በመጪው የክረምት ወቅት ለተከላ የሚውል ከ1 ነጥብ 6 ቢሊዮን በላይ ችግኝ እየተዘጋጀ መሆኑ ተገልጿል። በምክትል ርዕሰ መስተዳደር ማዕረግ የገጠር ልማት ዘርፍ አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ሀላፊ ዶክተር ድረስ ሳህል እንደገለጹት፤ በክልሉ ህዝቡን በስፋት በማሳተፍ በተከናወነ የአረንጓዴ አሻራ ችግኝ ተከላ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣት ተችሏል። በተለይ ባለፉት አምስት ዓመታት በተደረገ የችግኝ ተከላና እንክብካቤ ርብርብ የክልሉ የደን ሃብት ትርጉም ባለው መንገድ መሻሻሉን ገልጸዋል። በ2008 ዓ.ም የክልሉ የደን ሽፋን ከ10 በመቶ ያልበለጠ እንደነበር አስታውሰው፤ በቅርቡ በተደረገ ጥናትና በብሔራዊ ቆጠራ (ናሽናል ሴንሰስ) መሰረት የደን ሽፋኑ 16 በመቶ ላይ እንደደረሰ መረጋገጡን አስታውቀዋል። የአረንጓዴ አሻራ የችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር ውጤት ለውጥ እየታየበት ያለ ተግባር በመሆኑም ህዝብን ባሳተፈ አግባብ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ገልጸዋል። በቀጣዩ የክረምት ወቅትም ከአንድ ነጥብ ስድስት ቢሊዮን በላይ ችግኝ በማፍላት የተከላ ስራ ለማከናወን ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የደን ሃብት ልማት ስራው ሁሉም አካል ሃላፊነት ወስዶ ሊሰራበት የሚገባ ተግባር በመሆኑም መጪው ክረምት ለችግኝ ተከላ መርሃ ግብር መሳካት ሁሉም ሊረባረብ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። ''በየዓመቱ የሚከናወነው የችግኝ ተከላ የደን ሽፈንን ከማሳደጉም በላይ ለሌሎች የግብርና ስራዎች ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ ነው'' ያሉት ደግሞ በግብርና ቢሮው የተፈጥሮ ሃብት ልማትና ጥበቃ አጠቃቀም ዳይሬክተር አቶ እስመለዓለም ምህረት ናቸው።   የችግኝ ተከላ ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቅሰው፤ በመጪው ክረምት ለሚከናወነው የችግኝ ተከላም ከወዲሁ ዝግጅት እየተደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ለችግኝ ተከላውም ከ201 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለመሸፈን መታቀዱንና እስካሁን በተደረገ ጥረት ከ135 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ለተከላ ተለይቶ መዘጋጀቱን አስታውቀዋል። እንደ ዳይሬክተሩ ገለፃ፤ እስካሁን ባለው መረጃ ከግማሽ ቢሊዮን በላይ ችግኝ ተፈልቶ እንደተሰናዳ በቆጠራ ተረጋግጧል።  
በሚያዚያና ግንቦት ወር የበልግ ዝናብ ተጠናክሮ ይቀጥላል - የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት
Apr 5, 2024 559
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 27/2016(ኢዜአ)፦ በሚያዚያና ግንቦት ወር የበልግ ዝናብ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ገለጸ። ኢንስቲትዩቱ ባለፉት ሁለት የበልግ ወራት የነበረውን የአየር ጠባይ ግምገማና በሚቀጥሉት የበልግ ወራቶች የሚጠበቀው አየር ጠባይ አዝማሚያን በተመለከተ ዛሬ መግለጫ ሰጥቷል። በመግለጫውም፤ ባለፉት ሁለት የበልግ ወራት የበልግ ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑት በደቡብ፣ ደቡብ ምሰራቅና ሰሜን ምስራቅ የአገሪቱ አከባቢዎች ላይ ከመደበኛ በላይ የሆነ ዝናብ መጠንና ሥርጭት እንደነበር ተጠቅሷል። በሚያዚያና ግንቦት ወርም የበልግ ዝናብ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የአየር ትንበያ መረጃዎች እንደሚያሳዩ ኢንስቲትዩቱ ገልጿል። ይህንንም ተከትሎ በልግ ዋነኛ የዝናብ ወቅታቸው በሆኑ የደቡብና ደቡብ ምስራቅ የአገሪቱ አከባቢዎች ላይ ከመደበኛ በላይ ዝናብ እንደሚኖራቸው ተመላክቷል። የምዕራብ አጋማሽ መደበኛና ከመደበኛ በላይ የሰሜን ምስራቅ መካከለኛውና የምስራቅ የአገሪቱ አከባቢዎች መደበኛና ከመደበኛ በላይ ዝናብ ሊያገኙ እንደሚችሉም ትንበያው አሳይቷል። ኅብረተሰቡም ይህንን የአየር ጠባይ ትንበያ ከግምት በማስገባት የሚገኘውን ዝናብ ለግብርና እንቅስቃሴ ማዋል እንደሚገባና ሌሎች ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎችን ከባለሙያ ጋር በመመካከር ማካሄድ እንደሚገባ ተመላክቷል።    
በክልሉ ዘንድሮ ከ159 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች ተከናውነዋል
Apr 5, 2024 569
ዲላ ፤ መጋቢት 27/2016 (ኢዜአ)፡- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በዘንድሮ የተፋሰስ ልማት ከ159 ሺህ ሄክታር በሚበልጥ መሬት ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች መከናወናቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ። በህዝብ ተሳትፎ በለሙ አካባቢዎች ቡናን ጨምሮ ከ372 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት መደረጉም ተመላክቷል።   የቢሮው ሃላፊ አቶ ሃይለማርያም ተስፋዬ ለኢዜአ እንደገለጹት የዘንድሮው የተቀናጀ የተፋሰስ ልማት የተራቆቱና ተራራማ አካባቢዎችን ማዕከል በማድረግ ነው የተከናወነው። በክልሉ ሁሉም አካባቢዎች በላቀ የህዝብ ተሳትፎ የተከናወነው የልማት ሥራ ለ30 ቀናት የተካሄደ ሲሆን በዚህም ከ159 ሺህ ሄክታር በላይ ለጉዳት የተጋለጠ መሬት እንዲለማ መደረጉን ሃላፊው ገልጸዋል። በተፈጥሮ ሀብት ልማትና ጥበቃ ሥራው የጠረጴዛ እርከንን ጨምሮ የአፈር መከላትና መሸርሸርን የሚቀንሱ የተለያዩ ሥነ አካላዊ ሥራዎች መከናወናቸውንም ነው የገለጹት።   በልማት ሥራው ህብረተሰቡ በጉልበትና በተለያዩ መንገዶች ተሳትፎ ማድረጉንም አቶ ሀይለማርያም ገልፀዋል። እንደሳቸው ገለጻ፣ በዘመቻው የአፈርና ውሃ ጥበቃ በተከናወነባቸው አካባቢዎች ቡናና ፍራፍሬን ጨምሮ የተለያየ ጠቀሜታ ያላቸው ከ372 ሚሊዮን በላይ ችግኞችን ለመትከል ዝግጅት ተደርጓል። በዘንድሮ የአረንጓዴ አሻራ መርሃግብርም ህብረተሰቡን በነቂስ በማነቃነቅ በለሙ ተፋሰሶች ላይ የችግኝ ተከላ ሥራ እንደሚከናወን ተናግረዋል። የወላይታ ዞን ግብርና መምሪያ የተፈጥሮ ሀብት ዘርፍ ኃላፊ አቶ መስፍን መድኔ በበኩላቸው በዞኑ በ361 ንዑስ ተፋሰሶች ላይ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። በዚህም 76ሺህ 973 ሄክታር መሬት ለማልማት መቻሉን የገለጹት አቶ መስፍን፣ የለማው መሬት በስነ ሕይወታዊ ሥራዎች በማጠናከር ለግብርና ልማት ሥራ ይውላል ብለዋል።   በጌዴኦ ዞን ኮቸሬ ወረዳ ግብርና ጽህፈት ቤት የተፈጥሮ ዘርፍ ኃላፊ አቶ መክብብ መኮንን በበኩላቸው በልማቱ እርከንና የጉድጓድ ቁፋሮን ጨምሮ የተለያዩ የአፈርና ውሃ እቀባ ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። በህዝብ ተሳትፎ የቡና ጉንደላ፣ የቡና መትከያ ጉድጓድ መቆፈርና የተለያዩ ተግባራት በልማቱ መከናወናቸውን አመልክተዋል። በወረዳው የብሎያ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር በግዱ ጀጎ በተቀናጀ የተፋሰስ ልማት ሥራ በየዓመቱ እንደሚሳተፉ ገልጸዋል። ልማቱ እሳቸውን ጨምሮ የወረዳውን አርሶ አደሮች በተለያየ መንገድ ተጠቃሚ እያደረገ በመሆኑ በዘንድሮ የተፋሰስ ልማት ሥራ መሳተፋቸውን ተናግረዋል። በተለይ በተራቆቱ አካባቢዎች ካከናወኗቸው የመኖ ሣር ተከላ፣ ክትርና፣ ጉድጓድ መቆፈር ሥራዎች በተጨማሪ ሰው ሰራሽ ማዳበሪያ ሲያዘጋጁ መቆየታቸውን ገልጸዋል። በዘመቻው የእርከንና የጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ በተከናወነባቸው አካባቢዎች በአሁኑ ወቅት እየጣለ ያለውን የበልግ ዝናብ በመጠቀም እንሰት፣ ቡና እና ፍራፍሬ መትከል እንደጀመሩም ተናግረዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም