ፖለቲካ
መገናኛ ብዙሃን ሀገርን የሚገነቡ ተሻጋሪ ትርክቶች ላይ በትኩረት መስራት አለባቸው - አቶ ዛዲግ አብርሃ
Jul 16, 2025 115
  አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 9/2017(ኢዜአ)፦ መገናኛ ብዙሃን ሀገርን የሚገነቡ ዘመን ተሻጋሪ ትርክቶችን የመቅረጽ ሚናቸውን በተገቢው ሁኔታ መወጣት እንዳለባቸው የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት አቶ ዛዲግ አብርሃ ገለጹ። የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት አቶ ዛዲግ አብርሃ ለኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት(ኢዜአ) አመራሮች እና ጋዜጠኞች ስልጠና እየሰጡ ይገኛል። አቶ ዛዲግ መገናኛ ብዙሃን መረጃን ከማቅረብ ባሻገር መሰረታዊ ለውጥን የሚያመጡ ስራዎችን ማከናወን እንደሚገባቸው ገልጸዋል። በዚህ ረገድ መገናኛ ብዙሃን ሀገርን ለመገንባትና ዜጎችንም ለጋራ ሀገራዊ ግብ በአንድነት እንዲቆሙ የሚያስችሉ የይዘት ስራዎች ላይ ማተኮር አለባቸው ብለዋል።   መገናኛ ብዙሃን ለሀገር ግንባታ ቁልፍ ሚና የሚጫወቱ መሆናቸውን ጠቅሰው የግንባታ ሂደቱን ከማሳለጥ አኳያ ገንቢ ሚና መጫወት እንዳለባቸው አንስተዋል። ጋዜጠኞችም ከዕለት ደራሽ ዜና ባለፈ አዎንታዊ ተጽእኖ የሚፈጥር ይዘት ሰርቻለሁ ወይ? በሚል ራሳቸውን በመፈተሽ ዘላቂነት ላላቸው ጉዳዮች ትኩረት መስጠትና ራሳቸውን ማብቃት እንደሚኖርባቸው አመልክተዋል። መገናኛ ብዙሃን ችግር ነቃሽ ብቻ ሳይሆኑ መፍትሄ አፍላቂ መሆን ይገባቸዋል ያሉት ፕሬዝዳንቱ ለዚህም የጋዜጠኝነት ገንቢ ስራ አስተዋጽኦ እንዳለው ተናግረዋል። የመገናኛ ብዙሃን ዘገባዎች ዜጎች ላይ ተስፋን የሚጭሩ እና ብርሃን የሚያሳዩ መሆን እንዳለባቸውም ተናግረዋል። ድልድይ ሰዎችን እንደሚያገናኘው ሁሉ ትርክት የሰዎችን አዕምሮ ያገናኛል ያሉት ፕሬዝዳንቱ መገናኛ ብዙሃና የጋራ ትርክት ላይ በማተኮር ሀገር እና መንግስት ተቀራርበው እንዲሰሩ ምቹ መደላልድል መፍጠር እንደሚገባቸው አንስተዋል። ዘመን ተሻጋሪ የሚሆኑ ትርክቶችን በመቅረጽ፣ የህዝብ ድምጽ በመሆን እና ተቋማትን በማጠናከር ረገድ ጋዜጠኞች ወሳኝ ሚና አላቸው ብለዋል።   በተለይም ዜጎችን ትክክለኛ እና እውነተኛ መረጃ በማስታጠቅ እና ንቃተ ህሊናቸውን በማሳደግ ለሀገራቸው ጥቅም እና ፍላጎት እንዲቆሙ የማድረግ ትልቅ ኃላፊነት አለባቸው ነው ያሉት። ጋዜጠኛው ለፈተናዎች እና ለችግሮች እጅ ሳይሰጥ በአይበገሬነት በመስራት ሀገርን የሚገነቡ እና ትውልድን የሚቀርጹ ስራዎችን ማከናወን እንዳለባት አሳስበዋል።
ለሰባተኛው ሀገራዊ ምርጫ የዕጩዎችና መራጮች ምዝገባ በቴክኖሎጂ ታግዞ እንዲካሄድ የሚያስችል አሰራር ተዘጋጅቷል
Jul 16, 2025 114
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 9/2017(ኢዜአ)፦ለሰባተኛው ዙር ሀገራዊ ምርጫ የዕጩዎችና መራጮች ምዝገባ በምርጫ ጣቢያዎች በአካል ተገኝተው ከማካሄድ በተጨማሪ በቴክኖሎጂ ጭምር እንዲካሄድ አሰራር መዘጋጀቱን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ አስታወቀ። ቦርዱ የምርጫ ጣቢያዎች ስያሜዎች ደረጃቸውን የጠበቁና ወጥነት ያላቸው እንዲሆኑም እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰባተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ነፃ፣ ገለልተኛና ፍትሃዊ በሆነ መልኩ ለማካሄድ የተለያዩ ዝግጅቶችን እያደረገ ነው። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሜላተወርቅ ኃይሉ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንዳሉት ሰባተኛው ዙር አገራዊ ጠቅላላ ምርጫ ከቀደሙት ምርጫዎች በተሻለ መልኩ ለማካሄድ ከህግ-ማሻሻል ጨምሮ ሌሎች ዝግጅቶች እየተደረጉ ናቸው። በፖለቲካ ፓርቲዎች አስተዳደርና የምርጫ ስርዓት ማስፈጸሚያ አዋጅ ላይ ባለድርሻ አካላትን ያሳተፈ ጥናት መካሄዱንም ነው ያነሱት። ቀደም ሲል በተካሄዱ ምርጫዎች ሲካሄድ የነበረው የመራጮችና የዕጩዎች ምዝገባን በቴክኖሎጂ በመታገዝ ጭምር እንዲካሄድም አሰራር መዘጋጀቱን ተናግረዋል። እንደእርሳቸው ገለጻ፤ የመራጮችና የዕጩዎች ምዝገባ በምርጫ ጣቢያ በአካል ተገኝተው ከመመዝገብ በተጨማሪ ስማርት ስልክና ታብሌትን በመሳሰሉ ቴክኖሎጂዎች ለማካሄድ አማራጮች ተዘጋጅተዋል። የማሻሻያ አዋጁ የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን አካቶ እንዲፀድቅም ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቅረቡን አስታውቀዋል። የምርጫ ጣቢያዎችን ለመራጮች ምቹና ተደራሽ ከማድረግ ባለፈ የምርጫ ጣቢያዎች ስያሜ ደረጃውን በጠበቀ መልኩ እንዲሰየም ዝግጅቶች መደረጋቸውን ነው ሰብሳቢዋ የተናገሩት። በዚህም የምርጫ ጣቢያዎችን የማደራጀት ስራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይም በእያንዳንዱ ምርጫ ጣቢያ መሰረተ ልማትና ግብዓት የማሟላት ሥራ እንደሚቀጥል አመልክተዋል። ቦርዱ በአገራዊ ምርጫው ላይ በቂ ግንዛቤ እንዲያዝ እየሰራ መሆኑን ነው ሰብሳቢዋ የገለጹት። የፖለቲካ ፓርቲዎች መርሃ ግብሮቻቸውን ለመራጩ ህዝብ በተገቢው መንገድ እንዲያቀርቡ በቂ ስልጠና መስጠቱንም እንዲሁ። የፖለቲካ ፓርቲዎች በመረጃ ላይ የተመሰረተ መራጭ እንዲኖራቸው መርሃ ግብሮቻቸውን የሚያስተዋውቁበት ይፋዊ መድረክ በቅርቡ እንደሚጀምሩም ጠቁመዋል።  
ተለዋዋጭና ኢተገማች በሆነ ዓለም-ዓቀፋዊ የደኅንነት አውድ ውስጥ ሀገርን ማፅናት ያስቻሉ ስምሪቶች ተካሒደዋል
Jul 16, 2025 140
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 9/2017(ኢዜአ)፦ተለዋዋጭና ኢተገማች በሆነ ዓለም-ዓቀፋዊ የደኅንነት አውድ ውስጥ ሀገርን ማፅናት ያስቻሉ ስምሪቶች ማካሄዱን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አስታወቀ። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የ2017 በጀት አመት ዕቅድ አፈጻጻም ሪፖርት እና የ2018 በጀት ዓመት የዕቅድ አቅጣጫ ላይ ግምገማዊ ውይይት ማካሄዱን አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ለኢዜአ የላከው መግለጫ አመልክቷል። የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ስትራቴጂክ አመራሮች በተገኙበት መድረክ በተካሄደው ውይይት በ2017 በጀት ዓመት ተለዋዋጭና ኢተገማች በሆነ ዓለም-ዓቀፋዊና ቀጣናዊ የደኅንነት አውድ ውስጥ ጫናዎችን በመቋቋም ሀገርን ማፅናት ያስቻሉ ስምሪቶች እና የኦፕሬሽን ሥራዎች መከናወናቸው በመግለጫው ተጠቁሟል። በበጀት ዓመቱ ተቋሙ የተሰጠውን መረጃ የመሰብሰብና የመተንተን ተልዕኮ ከመወጣት አንፃር ስትራቴጂክ፣ ኦፕሬሽናልና ለፖሊሲ ግብዓት የሚሆኑ መረጃዎችን በማመንጨት ለውሳኔ ሰጪ አካላት ግብዓት እንዲሆኑ ማድረግ መቻሉ ተገልጿል።   የተሰበሰቡ መረጃዎችን መሰረት በማድረግ ከሌሎች የፀጥታና መረጃ ተቋማት ጋር በመቀናጀት የሕግ የበላይነትንና ተጠያቂነትን ማስፈን የሚያስችሉ የኦፕሬሽን ሥራዎች ተከናውነዋል፡፡ በተለያዩ ሕገ-ወጥ እንቅስቃሴዎች የተሳተፉና ከብሔራዊ ደኅንነትና ጥቅም በተጻራሪ የተሰለፉ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ተደርጓል። ይህን ተከትሎም አሁን ላይ በአንዳንድ የሀገሪቱ ክፍሎች የነበሩ የፀጥታ ችግሮች እየተፈቱ መሠረታዊ መሻሻሎች ታይተዋል። በሀገሪቱ የተካሄዱ በርካታ ዓለም-አቀፍና አህጉራዊ ጉባኤዎችን እንዲሁም የአቪዬሽን ደኅንነትን በማረጋገጥ ረገድ ምንም አይነት ክፍተት እንይፈጠር አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ውጤታማ ስምሪት ማካሄዱን መግለጫው አመልክቷል።   አገልግሎት መስሪያ ቤቱ የሥነ- ልቦና ጦርነትን ለመምራት እና ለማስተባበር በሕግ የተሰጠውን ኃላፊነት መሰረት አድርጎ ከውስጥ እና ከውጭ ሀገራችንን እና የሀገራችንን ብሔራዊ ጥቅም እንዲሁም ብሔራዊ ደኅንነትን ኢላማ አድርገው የተቃጡ ጦርነቶችን የመመከት፣ የመከላከል እና አስፈላጊ ሲሆንም የማጥቃት እርምጃዎችን በመውሰድ ረገድ ስኬታማ ተግባር ማከናወኑ በመግለጫው ተጠቅሷል። በበጀት ዓመቱ አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ባከናወናቸው ሥራዎች እንደ ተቋም መረጃን የመሰብሰብ፤ የመተንተን እና የመመዘን አቅምን ማሳደግ የተቻለበት፤ ብሔራዊ ጥቅምን ሊያስጠብቁ የሚያስችሉ ቀጣናዊና ዓለም አቀፋዊ ስምሪቶች የተከናወኑበት፤ ቴክኖሎጂን መታጠቅ ብቻ ሳይሆን በራስ አቅም ማላመድና ማበልፀግ ላይ ውጤት የተገኘበት እንዲሁም ሀብትን አቀናጅቶ መጠቀም ልምድ የዳበረበት መሆኑ እንደ ጥንካሬ ተነስቷል።   ባለፉት ዓመታት ትኩረት ተሰጥቷቸው በተከናወኑ የሪፎርም ሥራዎች በአሰራር ስርዓት የዘመነ፤ የሰለጠነ የሰው ኃይል የያዘና ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂ የታጠቀ እንዲሁም ኢትዮጵያን የሚመስል ተቋም ለመገንባት የተደረገው ጥረት ውጤት የተገኘበት እንደነበር ተገምግሟል። የመረጃና ደኅንነት ስምሪት ከተለዋዋጭ ሁኔታዎች ጋር ተጣጥሞ መካሄድ ስላለበት በቀጣይ የሪፎርም አጀንዳዎችን መከለስና ወቅቱን የሚዋጁ አዳዲስ አቅጣጫዎችን መስቀመጥ እንደሚገባ በመድረኩ ተጠቁሟል። በሚቀጥለው ዓመትም የሀገሪቱን የፀጥታ ሁኔታ ሙሉ ለሙሉ ወደ ተሟላ ሰላምና መረጋጋት መለወጥ፤ ለሀገራዊ ምርጫ ምቹ መደላድልን መፍጠር፤ ተለዋዋጭ ለሆኑ ሁኔታዎች ስትራቴጂካዊ ዝግጁነትን ማጠናከር ዋናዎቹ የትኩረት አቅጣጫ መሆናቸው ተነስቷል፡፡ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት በቀጣይ ዓመት እንደ ሀገር የሚከወኑ ሁነቶችን ተከትሎ ከውስጥና ከውጭ የሚሰነዘሩ የደኅንነት ስጋቶችን መቀልበስ የሚያስችል የሰው ኃይል፣ የቴክኖሎጂና የሎጀስቲክስ ቁመና ላይ እንደሚገኝ በመድረኩ መገምገሙን አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ አስታውቋል።
‎የሲዳማ ክልል ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ አዋጆችን እና ሹመት በማፅደቅ ተጠናቀቀ
Jul 16, 2025 64
‎ሀዋሳ ፤ ሐምሌ 9/2017(ኢዜአ) ፡- የሲዳማ ክልል ምክር ቤት 9ኛ መደበኛ ጉባኤውን የተለያዩ አዋጆችን እና ሹመት በማፅደቅ አጠናቀቀ ። ምክር ቤቱ የቀረበለትን የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ሰራተኞች ረቂቅ አዋጅ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል ። ‎አዋጁ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የተሰጣቸውን ተልዕኮ በአግባቡ እንዲወጡ፣ በሰራተኞች መካከል ፍትሀዊና አዎንታዊ ውድድር እንዲኖር ሚና ያለው እንደሆነ ተገልጿል ።   ‎በሌላ በኩል የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት አስፈፃሚ አካላት ማቋቋሚያ ፤ ሥልጣንና ተግባር መወሰኛ ረቂቅ አዋጅ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል ። ‎አዋጁ በሀገርና በክልል ደረጃ ያለውን ለውጥ መነሻ በማድረግ ተቋማት ለህብረተሰቡ የሚሰጡት አገልግሎቶች ተደራሽና አካታች እንዲሆኑ ብሎም ተግባራቸውን በቅንጅት እንዲፈፅሙና ሀብትን በአግባቡ መጠቀም እንዲችሉ ታሳቢ ያደረገ መሆኑ ተጠቅሷል ። ‎ምክር ቤቱ የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አደረጃጀት ሥልጣን እና ተግባር ለመወሰን የወጣ ረቂቅ አዋጅንም እንዲሁ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል ። ይህም ፖሊስ የተሰጠውን ሕገመንግስታዊ ተልዕኮውን በብቃት እንዲወጣ የሚያስችለው እንደሆነ ተጠቁሟል። ‎በተጨማሪም የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የሀዋሳ ከተማ መዋቅራዊ የውስጥ አደረጃጀትን መልሶ ለማዋቀር የቀረበውን ረቂቅ አዋጅም አፅድቋል ። ‎በዚህም የሀዋሳ ከተማ በአምስት ክፍለ ከተሞችና 26 ቀበሌዎች የሚዋቀር መሆኑ ተመለክቷል። ምክር ቤቱ የቀረቡለትን የተለያዩ ሹመቶችን አፅድቋል ። በዚህም መሰረት ፡- 1/አቶ ቢኒያም ሰለሞንን የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የፍርድ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ፣ 2/አቶ ገነነ ሹኔን የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የአስተዳደር ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ፣ 3/ አቶ ፍቅረየሱስ አሸናፊን የክልሉ የመሬት አስተዳደርና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ 4/ አቶ ዳዊት ዳንጊሶን የክልሉ ሠላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አድርጎ የሾመ ሲሆን፤ ተሿሚዎቹ በምክር ቤቱ አባላት ፊት ቀርበው ቃለ መሀላ ፈፅመዋል ።የምክር ቤቱ ጉባኤ መረሃ ግብሩን በዚሁ አጠናቋል።
በራስ ፀጋ የምግብ ሉዓላዊነትን እና ሁለንተናዊ እድገትና ብልጽግናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ዘርፈ ብዙ ተግባራት ተከናውነዋል
Jul 16, 2025 103
ድሬደዋ፣ ሐምሌ 09/2017(ኢዜአ ) በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በራስ ፀጋ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥና ሁለንተናዊ እድገትና ብልጽግናን ማረጋገጥ የሚያስችሉ ዘርፈ ብዙ ተግባራት መከናወናቸውን የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል ገለጹ። በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በመንግስት እና በፓርቲ ትብብር የተከናወኑ አበይት ተግባራትን የሚገመግም መድረክ በድሬደዋ እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንትና በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ኃላፊ አቶ አደም ፋራህን ጨምሮ የብልፅግና ፓርቲ ዋና መስሪያ ቤት እና የቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት አመራሮች፣ ሚኒስትሮች እና የየክልሎች ከፍተኛ አመራሮች ተገኝተዋል።   ከተረጅነት የመውጣት ጥረት፣ የስራ ዕድል ፈጠራ፣ የገበያ ማረጋጋትና የኑሮ ውድነትን በመቀነስ ረገድና ሌሎችም ጉዳዮችን በመዳሰስ የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራትና የተመዘገቡ ውጤቶችን በተመለከተ በስፋት ውይይት ተደርጓል።   በዚሁ ጉዳይ ላይ ማብራሪያ የሰጡት የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚል፤ ለዜጎች በውጭና ሀገር ውስጥ የስራ እድል በማመቻቸትና በመፍጠር ረገድ የተሳካ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። በኢትዮጵያ ክህሎት መር የስራ ዕድል ፈጠራ እንዲኖር በማድረግ ዜጎች በቀሰሙት ዕውቀትና ክህሎት ለሀገር ከፍታና ብልፅግና መረጋገጥ የድርሻቸውን እንዲወጡ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል። ከስራ እድል ፈጠራም ባለፈ በሌሎች ዘርፎች ተጨባጭ ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተው በቀጣይ በተጠናከረ መልኩ የሚቀጥል መሆኑን አረጋግጠዋል። በብልፅግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ ሰማ ጥሩነህ (ዶ/ር)፤ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ከተረጂነት ለመውጣት እና በራስ ፀጋ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በፓርቲና በመንግስት ትብብር የተከናወኑ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን አንስተዋል። በመሆኑም የተገኘውን ውጤት በማስቀጠል በተያዘው በጀት ዓመትም የላቀ አፈፃፀም እንዲኖር የተቀናጀ ጥረት ይደረጋል ብለዋል።   የንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስትር ዴኤታ አብዱልሃኪም ሙሉ(ዶ/ር)፤ በበኩላቸው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በማድረግ የሀገሪቱን ዘርፈ ብዙ ልማትና እድገት ማሳለጥ መቻሉን አንስተዋል።   የገበያ መረጋጋት እንዲኖር በመስራት የኑሮ ውድነትን በማረጋጋት ረገድ በስፋት ጥረት መደረጉንም ተናግረዋል።
በክልሉ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተመዘገቡ ስኬቶችን ህዝብን ተጠቃሚ ባደረገ መልኩ ይበልጥ ለማጠናከር ይሰራል - አቶ ሽመልስ አብዲሳ
Jul 15, 2025 141
አዳማ፤ ሐምሌ 8/2017(ኢዜአ)፦ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተመዘገቡ ስኬቶችን ህዝብን ተጠቃሚ ባደረገ መልኩ ይበልጥ ለማጠናከር ይሰራል ሲሉ የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ ተናገሩ። በኦሮሚያ ክልል የተሻለ አፈፃፀም ላስመዘገቡ በየደረጃው ለሚገኙ አመራሮችና መዋቅሮች እውቅና ተሰጥቷል። እውቅናው የተሰጠው ላለፉት ሶስት ቀናት ሲካሄድ በቆየው የ2017 ዓ/ም የፓርቲና የመንግስት የስራ አፈፃፀም እና የ2018 ዓ/ም እቅድ አቅጣጫ የግምገማ መድረክ ማምሻውን ሲጠናቀቅ ነው። በወቅቱ አቶ ሽመልስ አብዲሳ እንዳሉት በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በሁሉም መስክ በሚባል ደረጃ ስኬታማ ስራ ማከናወን ተችሏል። ይህንን ጥንካሬ ለማስቀጠል በግምገማው የጥንካሬ እና የድክመት መንስኤዎችን በጥልቀት መርምረን በመለየት አቅጣጫ አስቀምጠናል ብለዋል።   በመሆኑም በአዲሱ በጀት ዓመት የጥንካሬ መሠረቶችን በማስፋት የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በሚደረው እንቅስቃሴ በየደረጃው ያለው አመራር በተነሳሽነትና በቁርጠኝነት ለመስራት እንዲዘጋጅ አሳስበዋል። እውቅናና ሽልማት ላገኙ መዋቅሮች የእንኳን ደስ አላችሁ በማለትም ባገኛችሁት ስኬት ሳትኩራሩ፣ ለበለጠ እንድትተጉ ሲሉ አስገንዝበዋል።   የክልሉ ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ በበኩላቸው በክልሉ መንግስት ሽልማትና እውቅና የተሰጠው በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ስራን በጥራትና በብዛት መፈፀም የቻሉ አካላትን ለማበረታታት ነው ብለዋል። በተለይ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ በሁሉም የልማት መስኮች፣ በፀጥታና በመልካም አስተዳደር፣ በገቢ አሰባሰብና በተለያዩ ኢኒሼቲቮች ህብረተሰቡን በተጨባጭ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አስረድተዋል። ዞኖች፣ ወረዳዎች፣ ከተሞችና ቀበሌዎች ካላቸው መዋቅራዊ አደረጃጀት አኳያ እርስ በእርሰ እንዲወዳደሩ ጥረት መደረጉንም ገልፀዋል። እውቅናና ሽልማቱ የተሻለ የሰሩትን ለማበረታታትና የአፈፃፀም ክፍተት ያለባቸው ደግሞ እንዲያስተካክሉ ማድረግን ያለመ ነው ብለዋል። በመሆኑም በበጀት ዓመቱ የተሻለ አፈጻጸም ላስመዘገቡ የገጠርና የከተማ ቀበሌዎችና ወረዳዎች፣ ዞኖች፣ ለከተሞችና የክልል ሴክተሮች እውቅናና ሽልማት መሰጠቱን አመልክተዋል። ይህም እውቅና በየደረጃው የህዝብን ዘላቂ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥና ጠንካራ መዋቅር ለመገንባት መነሳሳትንና የውድድር መንፈስን ለማጎልበት ያስችላል ነው ያሉት።
ለሽብር ተልዕኮ የተመለመሉ 82 የአይ ኤስ አባላት በቁጥጥር ስር ዋሉ
Jul 15, 2025 245
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 8/2017(ኢዜአ)፦ለሽብር ተልዕኮ የተመለመሉ 82 የአይ ኤስ አባላት በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አስታወቀ። የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ለኢዜአ በላከው መግለጫ እንዳመለከተው፤ በፑንትላንድ የሚንቀሳቀሰው የአይ ኤስ የሶማሊያ ክንፍ በተለያዩ ሀገራት እንዲሁም በኢትዮጵያ ለመስፋፋትና የሽብር ቡድኑን ሴሎች ለመመስረት የሚያደርገውን ጥረት በተመለከተ የመረጃ ስምሪትና ጥናት ሲደረግ ቆይቷል፡፡ የአይ ኤስ የሶማሊያ ክንፍ በኢትዮጵያ የሽብር መረብ ለመዘርጋት የሚያደርገውን ሙከራ በተመለከተ ከጅምሩ በመረጃና በማስረጃ ተደግፎ ጥብቅ ክትትል ሲያደርግ መቆየቱን በመግለጫው ያስታወቀው አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ፤ የሥጋት ደረጃውን በተመለከተ በየጊዜው ባከናወነው ግምገማ ተጋላጭነትን የሚያስከትሉና ወደ ብሔራዊ ደኅንነት ሥጋት የሚያድጉ ተጨባጭ ግኝቶች መለየታቸውን ጠቁሟል፡፡ እንደ መግለጫው፤ የተከናወነውን ተጨባጭ መረጃና ማስረጃ የማጠናቀር ሂደት ተከትሎ የሽብር ቡድኑ በፑንትላንድ አሰልጥኖ ወደ ተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ያሰማራቸው 82 ተጠርጣሪዎች ተለይተው ከፌዴራል ፖሊስና ከክልል የጸጥታ አካላት ጋር በመተባበር በቁጥጥር ስር ውለዋል፡፡ ከቡድኑ ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ያላቸውና ሁለንተናዊ ድጋፍ ሲያደርጉ የነበሩ ተጠርጣሪዎች መካተታቸውን በመግለጽ፤ በተለይ በዓለም-አቀፍ የሽብር ቡድኑ በመረጃ ክንፍ የተደራጁ እንዲሁም በፋይናንስና በሎጀስቲክ እገዛ ሲያደርጉ የነበሩ ግለሰቦች በሕግ ቁጥጥር ስር መዋላቸው በመግለጫው ተመላክቷል፡፡ የሽብር ቡድኑ የጥፋት ተልዕኮውን ለማስፋፋትና ምልመላ ለማከናወን የሃይማኖት ተቋማትንና ሃይማኖትን እንደ ሽፋን ይጠቀማል ያለው የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ መግለጫ፤ የሕዝብን አንድነትና ተከባብሮ የመኖር እሴት የሚሸረሽሩ ብሎም ለአመጽና ሁከት የሚያነሳሱ አስተምህሮዎችን ለማስፋፋት ሙከራ ሲደረግ እንደነበር በተጨባጭ ማስረጃ መረጋገጡን አስታውቋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በአዲስ አበባ፣ በኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ፣ አዳማ፣ ሃሮማያ፣ ሻሸመኔ፣ ባሌ፣ ጅማና ሻኪሶ ከተማ ዙሪያ፤ በአማራ ክልል ከሚሴ አካባቢ፤ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ስልጤ ዞንና ሃላባ ቁሊቶ ከተማ፤ በሶማሌ ክልል ጅግጅጋ ከተማና በሐረሪ ክልል በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን፤ ግለሰቦቹን ለመያዝ በተደረገው ስምሪት በየአካባቢው የሚገኘው ኅብረተሰብ ከደኅንነትና ከጸጥታ አካላት ጋር በመተባበር ያሳየው ተሳትፎ በመልካም አርዓያነት የሚጠቀስ እንደነበር የአገልግሎት መሥሪያ ቤቱ መግለጫ ጠቁሟል፡፡ በቁጥጥር ስር ያልዋሉ የሽብር ቡድኑ አባላት ላይ የሚደረገው ክትትል ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ያመለከተው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ኅብረተሰቡም በየአካባቢው ሰላምን የሚያደፈርሱና ስጋት ሊፈጥሩ የሚችሉ አጠራጣሪ ሁኔታዎችን ሲመለከት አንደ ሁልጊዜው ለሚመለከታቸው የደኅንነትና የጸጥታ አካላት ጥቆማ በማቅረብ የዜግነት ግዴታውን እንዲወጣ ጥሪ አቅርቧል፡፡
በሲዳማ ክልል እየተመዘገበ ላለው ለውጥ የክልሉ ምክር ቤት ሚናውን በመወጣት አስተዋጽዖ እያበረከተ ነው-አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደ
Jul 14, 2025 134
ሀዋሳ ፤ሐምሌ 7/2017 (ኢዜአ)፦በሲዳማ ክልል እየተመዘገበ ላለው ለውጥ የክልሉ ምክር ቤት ሚናውን በመወጣት ጉልህ አስተዋጽዖ እያበረከተ መሆኑን የክልሉ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ፋንታዬ ከበደ ገለጹ። የሲዳማ ክልል ምክር ቤት ስድስተኛ ዙር 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 9ኛ መደበኛ ጉባኤውን እያካሄደ ነው፡፡   የምክር ቤቱ ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ እንደገለጹት በክልሉ በልማትና በመልካም አስተዳደር ሥራዎች እየተመዘገቡ ባሉ ውጤቶች ላይ ምክር ቤቱ የሚጠበቅበትን አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል። ምክር ቤቱ የአስፈጻሚ አካላትን የሥራ አፈጻጸም ከመከታተል ባለፈ እስከ ታችኛው መዋቅሮች በመውረድ የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎች እየተከናወኑ ያሉበትን ሁኔታ እንደሚገመግም ተናግረዋል ፡፡ በተለይ የካፒታል ፕሮጀክቶች ያሉበትን ደረጃ የመገምገም እንዲሁም በአስፈፃሚ ተቋማት ላይ ድንገተኛ ክትትል የማድረግ ሥራ ምክር ቤቱ እንደሚያከናውን ጠቁመዋል። በዚህም ቀደም ሲል የካፒታል ፕሮጀክቶች ላይ ይታይ የነበረው የመጓተት ችግር እየተፈታ መምጣቱን አመልክተዋል። የፍትህ ስርዓቱን ለማጠናከር የሲዳማ ባህላዊ የዳኝነት ሥርዓት የሆነው "አፊኒ” በተደራጀ መንገድ እንዲመራ አዋጅና ሕጎችን በማውጣት ህብረተሰቡ ከመደበኛ የፍትሕ ሥርዐት በተጨማሪ እንዲጠቀምበት እየተደረገ መሆኑን አስታውቀዋል። የዳኝነት ሥርዐቱን በተሻለ ዕውቀት እንዲመሩም ከ568 ቀበሌያት ለተውጣጡ የባህል መሪዎች ሥልጠና መሰጠቱንም አፈ ጉባኤዋ ጠቁመዋል።   በክልሉ በዓመት ለሁለት ጊዜ ህዝባዊ ፎረሞች እንደሚደረጉ የገለጹት ወይዘሮ ፋንታዬ፣ በእዚህም ህብረተሰቡ የሚያነሳቸውን የመልካም አስተዳደር ቅሬታዎች ለይቶ በመገምገም ለመፍትሄው እንዲሰራ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል። ለአብነትም በዳራ ቀባዶ ሆስፒታል ተፈጥሮ የነበረውን የመልካም አስተዳደር ችግር ህዝባዊ የውይይት መድረክ በማዘጋጀት በተወሰደ እርምጃ ለማስተካከል መቻሉን ጠቅሰዋል። በኦዲት ግኝት 22 ሚሊዮን ብር የባከነ ገንዘብ ለማስመለስ እንደተቻለ ጠቁመው፣ 450 ሚሊዮን ብር የሚጠጋ በአሰራር ብልሽት ይባክን የነበረ ገንዘብም ለማስተካከልና ለማዳን መቻሉን ተናግረዋል። በጉባኤው ያለፈው የምክርቤቱ ስብሰባ ቃለ ጉባኤ የፀደቀ ሲሆን የምክር ቤቱ የበጀት ዓመቱ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርትም ቀርቦ ውይይት እየተደረገበት ነው ፡፡    
የጋራ ትርክትን በመገንባት የጋራ መፃኢ እጣ ፈንታን ለመወሰን በሚደረገው ሂደት የመገናኛ ብዙሃን ሚና የጎላ ነው-አቶ ዛዲግ አብርሃ
Jul 14, 2025 233
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 7/2017 (ኢዜአ)፦የጋራ ትርክትን በመገንባት የጋራ መፃኢ እጣ ፈንታ ለመወሰን በሚደረገው ሂደት የመገናኛ ብዙሃን ሚና የጎላ መሆኑን የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዚዳንት አቶ ዛዲግ አብርሃ ገለፁ። የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ) ከአፍሪካ አመራር ልህቀት ማዕከል ጋር በመተባበር በትርክትና በአገር ግንባታ የጋዜጠኝነት ሚናን የተመለከተ ስልጠና እየተሰጠ ይገኛል። ለአራት ቀናት በሚቆየው ስልጠና የኢዜአ የማዕከልና ክልል ቅርንጫፍ ቢሮ ኃላፊዎችና ሰራተኞች እየተሳተፉ ይገኛሉ።   የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዚዳንት አቶ ዛዲግ አብርሃ ስለትርክት ምንነት፣ አስፈላጊነት፣ የትርክት ኃይልና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በስልጠናው ትርክት ማንነትን ለመቅረፅ፣ሰዎችን ለማነሳሳት፣ ባህልን ለማሻገር እንዲሁም ውሳኔ ለመወሰን የሚጠቅም መሆኑን አንስተዋል። ትርክት ዓለምን የምናይበት መነፅር መሆኑ ጠቅሰው፤ ትርክቷን የዘነጋች አገር እንዴት መነሳት እንዳለባት አታውቅም ብለዋል።   ትርክት ማንነትን የሚቀርፅ መሆኑና አገር የሚወለደው በጋራ ትርክት እንደሆነም አቶ ዛዲግ ገልፀዋል። የጋራ ትርክትን መገንባት የጋራ መፃኢ እጣ ፈንታን ለመወሰን የሚያስችል መሆኑን ጠቁመው፤ ለጋራ ትርክት ግንባታ ሂደት የመገናኛ ብዙሃን ሚና የጎላ መሆኑንም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ በቀጣናው ያለውን ትብብር የበለጠ ለማጎልበት እየሰራች ነው
Jul 14, 2025 169
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 7/2017 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በቀጣናው ያለውን ትብብር የበለጠ ለማጎልበት እየሰራች መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አዳም ተስፋዬ ገለጹ። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ለቀጣናው ሀገራት የተለያዩ ሥልጠናዎችን በማዘጋጀት ትብብርን ይበልጥ ለማጎልበት እየሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ከኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ዩጋንዳ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ሶማሊያና ደቡብ ሱዳን ለመጡ ዲፕሎማቶች ለሶስት ቀናት የሚቆይ ሥልጠና መስጠት ጀምሯል።     የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ኃላፊ አዳም ተስፋዬ በሥልጠናው መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር ኢትዮጵያ በቀጣናው ትብብርን ይበልጥ ለማጎልበት እየሰራች ነው ብለዋል። ቀጣናው ሽብርተኝነት፣ ሕገወጥ ስደትና የጦር መሳሪያ ዝውውር እንዲሁም ሌሎች በተናጥል ሊፈቱ የማይችሉ ችግሮች ያሉበት መሆኑን አንስተዋል። ተግዳሮቶችን ለመፍታት ብዙ ጠቃሚ ተግባራት እየተከናወኑ ቢሆንም በቀጣይም ተጨማሪ እርምጃዎችን እንደሚጠይቅ ተናግረዋል። ስልጠናው ችግሮችን ለመፍታት የጋራ ጥበቦችን እና ቁርጠኝነት የሚጠናከርበት አንዱ ጠቃሚ ተግባር መሆኑንም ገልጸዋል። የቀጣናውን ትብብር ማጠናከር እና በህዝቦች መካከል ጥልቅ መግባባት መፍጠር በስልጠናው መርሃ ግብር ከተቀመጡ ተልዕኮዎች መካከል መሆኑንም ተናግረዋል። በጋራ ክልላዊ ተግዳሮቶች ላይ የትብብር መድረክን መፍጠር፣ በአፍሪካ ቀንድ ገንቢ ተሳትፎን ማበረታታት እና ማሳደግ ሌላኛው ዓላማ እንደሆነ አክለዋል። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት የስልጠና ክፍል ዳይሬክተር ጀነራል መላኩ ሙሉዓለም በበኩላቸው፤ ስልጠናው በጋራ በሆኑ ቀጣናው ጉዳዮች ላይ ያተኮረ እንደሆነ ተናግረዋል።   ስልጠናው በፓን አፍሪካኒዝም፣ ድንበር ተሻጋሪ ሃብቶችን በጋራ መጠቀምና ሰላም ማስከበር ጉዳዮች ላይ ትኩረት አድርጎ እየተሰጠ መሆኑን ተናግረዋል። ከኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ዩጋንዳ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ ሶማሊያና ደቡብ ሱዳን የመጡ ዲፕሎማቶች እየተሳተፉ እንዳለ ጠቅሰዋል።
በኢትዮጵያ የዳበረና የተረጋጋ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ለመገንባት የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አባላትን አቅም መገንባት ትኩረት ተሰጥቷል
Jul 14, 2025 166
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 7/2017 (ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ የዳበረና የተረጋጋ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ለመገንባት የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አባላትን አቅም ማጎልበት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝ ተገለጸ። የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት፣ የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚና የኔዘርላንድስ መልቲ ፓርቲ ዴሞክራሲ ኢንስቲትዩት በጋራ መስራት የሚያስችላቸውን የሦስትዮሽ ስምምነት ተፈራርመዋል።     የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ሰለሞን አየለ በመግባቢያ ስምምነቱ ሥነ-ሥርዓት ወቅት እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሥርዓትን ለማዳበር በዕውቀት ላይ የተመሰረተ አመራርና አባላትን አቅም መገንባት ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራር አባላትን አቅም ማጎልበት የሚያስችሉ ሥልጠናዎች ማዘጋጀት ወሳኝ ነው ብለዋል።   ምክር ቤቱ ከዚህ አኳያ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በጋራ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤ ከአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ጋርም መስራቱ በዕወቀት የሚመራ አመራር ለመገንባት ያለውን ቁርጠኝነት ያሳያል ብለዋል። የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዚዳንት ዛዲግ አብርሃ እንደገለጹት፤ በኢትዮጵያ የዳበረ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ሂደት ውስጥ የፖለቲካ ፓርቲ አመራር አባላትን አቅም ማሳደግ ወሳኝ በመሆኑ የልህቀት አካዳሚው ትኩረት ሰጥቶ ይሰራል።   ለዚህ ደግሞ አካዳሚው በአገር በአቀል ዕውቀት የታገዘ የፖለቲካ ፓርቲዎች የስልጠና መመሪያና የአመራር ልማት ግንባታ እቅድና ስትራቴጂ ማዘጋጀቱንም ገልጸዋል። የኔዘርላንድ መልቲ ፓርቲ ዴሞክራሲ ኢንስቲትዩት የኢትዮጵያ ተወካይ ይነበብ ንጋቱ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ ጠንካራ የመድብለ-ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ላይ የቴክኒክና የፋይናንስ ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ አንስተዋል።   በመድብለ ፓርቲ ስርዓት ውስጥ እየተገነባ ላለው ዴሞክራሲ ስርዓት ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ሲሰሩ መቆየታቸውን ገልጸው፤ ከልህቀት አካዳሚው ጋርም በጋራ ለመስራት የሚያስችላቸውን ስምምነት በዛሬው ዕለት መፈራረማቸውን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ጠንካራ የመድበለ-ፓርቲ ሥርዓት በመገንባት ሂደት በትብብር ለመስራት ዝግጁ መሆኑንም የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዚዳትንት ዛዲግ አብረሃ አረጋግጠዋል። የኢትዮጵያ ፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ሰለሞን አየለ በዚህ ረገድ ተቋማቱ በኢትዮጵያ የዳበረና የተረጋጋ የመድብለ-ፓርቲ ሥርዓት ለመገንባት የተፈራረሙትን ስምምነት ውጤታማ ለማድረግ አቅማቸውን አሟጠው እንደሚሰሩ ገልጸዋል።
በዓመቱ የኢትዮጵያን የተረጂነት ታሪክ ለመቀየር መሰረት የጣሉ ሥራዎች ተከናውነዋል - አቶ አደም ፋራህ
Jul 14, 2025 163
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 7/2017 (ኢዜአ)፦በ2017 በጀት ዓመት ከተረጂነት ለመውጣት የተከናወኑ ሥራዎች የኢትዮጵያን የተረጂነት ታሪክ ለመቀየር መሰረት የጣሉ ናቸው አሉ የብልጽግና ፓርቲ ም/ፕሬዚዳንትና የዋና ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አደም ፋራህ፡፡ የ2017 በጀት ዓመት የፓርቲው ሥራዎች ማጠቃለያ የግምገማ መድረክ በድሬዳዋ ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡ አቶ አደም ፋራህ በመድረኩ ባደረጉት ንግግር ፥ 2017 በጀት ዓመት በርካታ ሥራዎች የተከናወኑበት፣ የትጋት እና የስኬት ዓመት እንደነበር አንስተዋል፡፡ ፓርቲውን በሰብዓዊና በቁሳዊ ሃብት ለማጠናከር፣ በዘመናዊ መረጃ ለማደራጀት እንዲሁም ገዢ ትርክትና ቅቡልነትን ከማረጋገጥ አንጻር የተከናወኑ ሥራዎች ስኬታማ ናቸው ብለዋል። በአስተሳሰብ፣በአደረጃጀትና በአሰራር የተዋሃደ ፓርቲ ለመፍጠር የተሰሩ ሥራዎች ስኬታማ እንደነበሩ ጠቁመው፥ በዚህም የፓርቲውን 2ኛ መደበኛ ጉባዔና 5ኛ ዓመት ምስረታ በዓል በተቀናጀ መንገድ ማክበር ተችሏል ማለታቸውን የዘገበው ኤፍ ኤም ሲ ነው። የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ዕድገት ቀጣይነትና ዘላቂነት ያለው እንዲሆን በትኩረት መሰራቱን የተናገሩት አቶ አደም፥ በዚህም አመርቂ ውጤት መመዝገቡን አመልክተዋል፡፡ በንቅናቄ የተከናወኑ ሥራዎች ውጤታማ እንደነበሩ እና ሕዝቡ አካታች ሀገራዊ ምክክር ላይ እንዲሳተፍ በመደረጉ የምክክር ሒደት በተሳካ መንገድ መቀጠሉን አስገንዝበዋል፡፡ ገዢ ትርክትና ቅቡልነት እንዲረጋገጥ በተከናወነው ሥራ ሀገራዊ አንድነትን የሚያጎለብቱ አዎንታዊ ስኬቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል፡፡ በበጀት ዓመቱ የተመዘገቡ ድሎችን ማስቀጠልና የታዩ ክፍተቶችን በመቅረፍ ለሁለንተናዊ ብልጽግና መረጋገጥ ሕዝቡን በማሳተፍ መስራት እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡
ከተማ አስተዳደሩ የኮሪደር ልማትን ለሌሎች ከተሞች ተሞክሮ በማካፈል ሁሉን አቀፍ ብልፅግና ለማረጋገጥ እየሰራ ነው-ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 13, 2025 233
አሶሳ፤ሐምሌ 6/2017 (ኢዜአ)፦ከተማ አስተዳደሩ እያከናወነ የሚገኘውን የኮሪደር ልማት ለሌሎች ከተሞች ተሞክሮ በማካፈል ሁሉን አቀፍ ብልፅግና ለማረጋገጥ እየሰራ ነው ሲሉ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የአመራር ለአመራር ግንኙነትና ልምድ ልውውጥ መድረክ ዛሬ በአሶሳ ከተማ ተካሄዷል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አቤቤ በመድረኩ ላይ እንደተናገሩት፤ ከተማ አስተዳደሩ እያከናወነ የሚገኘውን የኮሪደር ልማት ለሌሎች ከተሞች ተሞክሮ በማካፈል ሁሉን አቀፍ ብልፅግና ለማረጋገጥ እየሰራ ነው። በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተከናወነ የሚገኘው የኮሪደር ልማት በአዲስ አበባ ከተማም በህብረተሰቡ ተሳትፎ እና በአመራሩ ቁርጠኝነት እየተከናወነ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ፕሮጀክቶችን በፍጥነት የማጠናቀቅ ተሞክሮን በማሳደግ የህብረተሰቡን ተጠቃሚነት ማሳደግ መቻሉንም ከንቲባዋ ተናግረዋል። የሚከናወኑ የልማት ስራዎች ዘላቂ እና የረጅም ጊዜ አገልግሎት እንዲሰጡ ተደርገው መሠራት እንዳለባቸውም ከንቲባዋ አስታውቀዋል። ​ በልማቱ ሂደት የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን ህብረተሰቡ ለራሱ መሆኑን ማስገነዘብ እና የባለቤትነት ስሜት እንዲኖረው ማድረግ እንደሚገባም አስረድተዋል። የአሶሳ ከተማ የኮሪደር ልማት የሥራ እንቅስቃሴን የጎበኙት ከንቲባዋ፥ የኮሪደር ልማቱ የከተማዋን ገፅታ የሚቀይር እና ለኢንቨስትመንት ተመራጭ የሚያደርጋት መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ የሚገኙ ባለሃብቶች በልማት ስራዎች ላይ ተሳታፊ እንዲሆኑ የቅርብ ግንኙነት በመፍጠር የልማት አሻራቸውን እንዲያሳርፉም በትብብር መሥራት ይጠበቃል ነው ያሉት። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በአሶሳ ከተማ የሚከናወኑ የልማት ስራዎችን ለማገዝ ዝግጁ መሆኑንም ከንቲባ አዳነች አቤቤ አረጋግጠዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን በበኩላቸው፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አመራሮች በክልሉ የልማት ሥራዎች ላይ እያደረጉት ለሚገኘው ድጋፍ አመስግነዋል። ከከተማ አስተዳደሩ የተገኙ ምርጥ ተሞክሮዎችን በመቀመር የክልሉን የመሠረተ ልማት ተደራሽነት ለማሳደግ እንደሚሰራም አረጋግጠዋል። በመድረኩ ላይ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል።
የሲዳማ ክልል ምክር ቤት 9ኛ መደበኛ ጉባኤውን ነገ ማካሄድ ይጀምራል
Jul 13, 2025 125
ሀዋሳ ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ የሲዳማ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ምርጫ ዘመን 4ኛ ዓመት 9ኛ መደበኛ ጉባኤውን ነገ ማካሄድ እንደሚጀምር የምክር ቤቱ ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ ገለጹ። ምክር ቤቱ ለሦስት ተከታታይ ቀናት በሚያካሄደው ጉባኤ በ11 አጀንዳዎች ላይ እንደሚወያይም ተመልክቷል። የምክር ቤቱ ዋና አፈ-ጉባኤ ወይዘሮ ፋንታዬ ከበደ ለኢዜአ እንዳሉት ምክር ቤቱ የ2017 በጀት ዓመት የማጠቃለያ መደበኛ ጉባኤውን ከነገ ጀምሮ ማካሄድ ይጀምራል። ምክር ቤቱ ከነገ ጀምሮ በሚያካሂደው 6ኛ ምርጫ ዘመን 4ኛ ዓመት 9ኛ መደበኛ ጉባኤውም በ11 አጀንዳዎች ላይ እንደሚወያይ ተናግረዋል። ከአጀንዳዎቹ መካከልም የምክር ቤቱን የ8ኛ መደበኛ ጉባኤ፣ የ2017 አፈጻጸም ሪፖርት፣ የ2018 ረቂቅ ዕቅድና በጀት ማፅደቅ እንደሚገኙበትም አፈ-ጉባኤዋ አመልክተዋል። በተጨማሪም ምክር ቤቱ የአስፈጻሚ መስሪያ ቤቶችን፣ የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤትና የኦዲት መስሪያ ቤቱ የ2017 ዓ/ም አፈጻጸም ሪፖርትና የ2018 በጀት ዓመት ረቂቅ ዕቅድና በጀት ቀርቦ ያጸድቃል ተብሎ እንደሚጠበቅም ተገልጿል። እንዲሁም በምክር ቤቱ ጉባኤ የተለያዩ አዋጆችና ሹመቶች ቀርበው እንደሚፀድቁም ዋና አፈ-ጉባኤዋ ተናግረዋል።  
በክልሉ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስኮች የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ተግባራት ተከናውነዋል - አቶ ሽመልስ አብዲሳ
Jul 13, 2025 135
አዳማ ፤ ሐምሌ 6/2017(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስኮች የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ተግባራት መከናወናቸውን የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ሽመልስ አብዲሳ አስታወቁ። የኦሮሚያ ክልል የ2017 በጀት ዓመት የመንግስትና የፓርቲ የስራ አፈፃፀም ግምገማ የክልሉ ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ፣ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አወሉ አብዲ፣ አፈጉባኤ ሰዓዳ አብዱረሃማንን ጨምሮ ሌሎች የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች በተገኙበት በአዳማ መካሄድ ጀምሯል።   የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት አቶ ሽመልስ አብዲሳ እንደገለፁት በክልሉ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መስኮች የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጡ ተግባራት ተከናውነዋል። የክልሉ መንግሥት የአርሶና አርብቶ አደሩን እንዲሁም የከተማ ነዋሪዎችን ኑሮ ህይወት ለማሻሻልና ለመለወጥ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። በተለይም በስራ እድል ፈጠራ፣ የመሬት አስተዳደርና አጠቃቀም በማዘመን፣ ገቢን በማሳደግና የአርብቶ አደሩን ህይወት መለወጥ በሚያስችሉ ተግባራት ላይ በትኩረት መሰራቱን ጠቅሰዋል። መድረኩ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የስራ አፈጻጸም በጥልቀት የሚፈተሽበትና ጠንካራና ደካማ ጎኖች ተለይተው ለ2018 በጀት ዓመት አቅጣጫ የሚያዝበት መሆኑን አመላክተዋል። በየደረጃው ያለው አመራርም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የተገኙ አበረታች ውጤቶችን በአዲሱ በጀት ዓመት በሙሉ አቅሙ አጠናክሮ ማስቀጠል እንደሚገባው አስገንዝበዋል። "አዲሱ የበጀት ዓመት ለህዝቡ ቃል የገባንበት ሁለንተናዊ የልማት መስኮች ለማሳካት በሙሉ አቅማችን የምንረባረብበት ዓመት በመሆኑ በየደረጃው ያለው አመራር ራሱን ማዘጋጀት አለበት" ሲሉም አክለዋል። ለአገልግሎት አሰጣጥ እንቅፋት ሊሆኑ የሚችሉ ብልሹ አሰራሮች፣ ሌብነት፣ ህገ ወጥ ንግድና ኮንትሮባንድ፣ የጎጠኝነትና የጥቅም ጥገኝነት አመለካከቶችና አስተሳሰቦችን ለማምከን መረባረብ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። በብልፅግና ፓርቲ የኦሮሚያ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ሃላፊ አቶ ከፍያለው ተፈራ በበኩላቸው የተጠናቀቀው በጀት ዓመት በመንግሥትና በፓርቲ ስራ የተሻለ ተግባር የተከናወነበት ነው ብለዋል።   በዚህም ጠንካራ የመንግስትና የፓርቲ አደረጃጀትና አሰራር ለመፍጠር አበረታች ስራዎች የተከናወኑበት መሆኑንም ተናግረዋል። የቀበሌ አደረጃጀትና መዋቅር በመዘርጋት በተለይም ህዝቡ በቅርበት አገልግሎት እንዲያገኝ ማስቻሉንም ጠቅሰዋል። በዚህም በክልሉ የተሻለ ሰላም በማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎች ማከናወን የተቻለበት መሆኑን አመልክተዋል።
የሀገር መከላከያ ሠራዊት በወታደራዊ ቴክኖሎጂ ፈጠራ ወደ ላቀ ደረጃ እየተሸጋገረ ነው - ሚኒስትር አይሻ መሐመድ(ኢ/ር)
Jul 12, 2025 284
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የሀገር መከላከያ ሠራዊት በወታደራዊ ቴክኖሎጂ ፈጠራ ወደ ላቀ ደረጃ እየተሸጋገረ እንደሚገኝ የመከላከያ ሚኒስትር አይሻ መሐመድ(ኢ/ር) ገለጹ። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ በምህንድስና፣ በጤና ሳይንስ፣ በቢዝነስ እና በኃብት አስተዳደር እንዲሁም በሌሎች የትምህርት መርኃ ግብሮች በመጀመሪያ፣ በሁለተኛ እና በሶስተኛ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ዛሬ አስመርቋል።   በምረቃ መርኃ ግብሩ የመከላከያ ሚኒስትር አይሻ መሐመድ(ኢ/ር)፣ የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)፣ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ እና የዩኒቨርሲቲው ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ፣ የመከላከያ ከፍተኛ መኮንኖች፣ የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎችና የተመራቂ ቤተሰቦች ተገኝተዋል። በምረቃ መርኃ ግብሩ ላይ የተገኙት የመከላከያ ሚኒስትር አይሻ መሐመድ(ኢ/ር) ለተመራቂዎች የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል። መንግሥት ዘመናዊ የሰራዊት ግንባታ እንዲሁም ወታደራዊ ቴክኖሎጂ ማፍለቅና ማምረት ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በዚህም በእውቀት፣ በዓላማ እና በሙያዊ ክህሎት የታነጹ ጀግና የሰራዊት አባላት እና ቴክኖሎጂ ፈጣሪዎችን እያፈራን ነው ብለዋል።   የሀገር መከላከያ ሠራዊት በወታደራዊ ቴክኖሎጂ ፈጠራ ወደ ላቀ ደረጃ እየተሸጋገረ እንደሚገኝ ጠቅሰው፥ የመከላከያ ዩኒቨርሲቲም የሰለጠነ የሠራዊት አባላትንና ሲቪል አመራር በማፍራት ላይ መሆኑን ጠቁመዋል። የሠራዊቱን የወታደራዊ ቴክኖሎጂ ብቃት ለማላቅ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው በተለይም ዘመናዊ የሰራዊት ግንባታን በቴክኖሎጂ ማገዝ የሚችሉ ብቁና ሥነ-ምግባር ያላቸውን ሙያተኞች እያፈራ መሆኑን ጠቁመዋል። ዩኒቨርሲቲው ለሀገርና ለመጪው ትውልድ የሚሻገር ስራ መሥራቱን አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ገልጸው፥ የምርምርና የማህበረሰብ አገልግሎትን በማስፋት እንዲተገብርም ተናግረዋል። በዘመናዊ የሠራዊት ግንባታ ሂደት እውቀትና ቴክኖሎጂ መሠረታዊ መሆኑን አንስተው ለዚህም ዩኒቨርሲቲው ከዚህ አኳያ አመርቂ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ተመራቂዎች በታማኝነት፣ በቅንነትና በስነምግባር ሀገራቸውን ማገልገል እንዳለባቸውም አፅንኦት ሰጥተዋል።   የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ብርጋዴር ጄኔራል ከበደ ረጋሳ፤ ዩኒቨርሲቲው በእውቀትና በክህሎት ብቁ የሆነ የሰው ኃይል እያፈራ መሆኑን ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲው የመከላከያ ሰራዊቱን የተልዕኮ አፈጻጸም ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግሩ ወታደራዊና ሲቪል አመራሮችን በማፍራት ላይ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በቴክኖሎጂው ዘርፍ ሀገርን የሚያሻግሩ ሥራዎች በመስራት ላይ እንደሚገኝ ጠቁመው የመከላከያን የሰለጠነ የሰራዊት ግንባታ በማገዝ ላይ መሆኑንም አንስተዋል። ኢትዮጵያ ከውጭ የምታስገባቸውን ወታደራዊ ቴክኖሎጂዎች በሀገር ውስጥ ለመተካት ዩኒቨርሲቲው የተለያዩ ስራዎችን በመሥራት ላይ መሆኑን አክለዋል።   ከዩኒቨርሲቲው ተመራቂዎች መካከል ሀምሳ አለቃ ንጋቱ ሞላ እና ፍራኦል ጉተማ በተማሩት የሙያ መስክ ሀገራቸውንና ህዝባቸውን በቅንነት ለማገልገል ዝግጁ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡   በቴክኖሎጂ ምርምር እና በጤናው ዘርፍ የሠራዊቱን አቅም ለማጎልበት እንደሚሰሩም ተናግረዋል፡፡ አስር አለቃ ሃብታሙ ሊበን በበኩሉ የሀገርን ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ ዝግጁ መሆኑን ገልጾ፥ እውቀቱን ለሌሎች የሰራዊቱ አባላት ለማካፈል ዝግጁ ነኝ ብሏል፡፡   በምርቃት መርኃ ግብሩ ላይ የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ ተመራቂዎች ሽልማት ተበርክቷል። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ በ2025 ከአፍሪካ አምስት ምርጥ የመከላከያ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ የመሆን ራዕይ ሰንቋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ የተለያዩ ሹመቶችን በማጽደቅ ተጠናቀቀ
Jul 12, 2025 200
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ምክር ቤት 4ኛ ዓመት የሥራ ዘመን 4ኛ መደበኛ ጉባኤ የተለያዩ ሹመቶችን በማጽደቅ ተጠናቋል፡፡ ምክር ቤት ለሁለት ቀናት ባካሄደው መደበኛ ጉባኤው የከተማ አስተዳደሩ የ2017 በጀት ዓመት ሪፖርት፣ የ2018 በጀት ዓመት አቅጣጫ፣ የ2018 ረቂቅ በጀት እና የተለያዩ አዋጆች ላይ በመወያየት አጽድቋል።   በተጨማሪም በአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የቀረቡ የተለያዩ ተቋማት ሃላፊዎችን ሹመት አጽድቋል። በዚህም መሰረት አቶ አብዱልቃድር ሬድዋን በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የፋይናንስ ቢሮ ሃላፊ፣ አቶ መኮንን ያኢ የመሬት ልማትና አስተዳደር ቢሮ ሃላፊ፣ አቶ ኦሊያድ ስዩም የከተማ ቦታ ማስለቀቅ ጉዳዩች እና ይግባኝ ሰሚ ጉባኤ ፕሬዝዳንት ሆነው ተሹመዋል። ምክር ቤቱ የአስፈፃሚ አካላት ስልጣንና ተግባር እንደገና ለመወሰን የቀረበውን ረቂቅ የማሻሻያ አዋጅ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል። የማሻሻያ ረቂቅ አዋጁ ውሳኔ፣ አስፈላጊነት፣ ዝርዝር ይዘት፣ ተሳትፎ፣ የሚያስገኘው ሃብት፣ የሚፈታው ችግር እንዲሁም ለከተማዋ ሁለንተናዊ እድገት ያለውን ተገቢነት ታሳቢ በማድረግ የተዘጋጀ መሆኑ ተገልጿል።   በዚህም መሠረት፦ - ከአዲስ አበባ የባህል ኪነ ጥበብና ቱሪዝም ቢሮ ተልዕኮዎች የቱሪዝም ዘርፉ ለብቻው የአዲስ አበባ ቱሪዝም ኮሚሽን ሆኖ ለከንቲባ ፅህፈት ቤት ተጠሪ በመሆን እንዲቋቋም፣ - የአዲስ አበባ ዲዛይንና ግንባታ ቢሮን ከትላልቅ ፕሮጀክቶች ግንባታ ፅህፈት ቤት ጋር እንዲዋሃድ፣ - የአዲስ አበባ ማህበራዊ ትረስት ፈንድ ፅህፈት ቤት ከህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፍቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ጋር እንዲዋሃድ እና - የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የከተማ ውበትና አረንጓዴ ልማት ቢሮ አንድ ተግባር በከፊል ለውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ማስተላለፍ ላይ የቀረበውን ማሻሻያ አዋጅ ምክር ቤቱ በመሉ ድምፅ አፅድቋል።
የመከላከያ ዩኒቨርሲቲ ብቁ ሰራዊት ከመገንባት በተጓዳኝ ወታደራዊ ቴክኖሎጂዎችን እየፈጠረ ነው - ብርጋዴር ጀነራል ከበደ ረጋሳ
Jul 12, 2025 187
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 5/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ብቁ ሰራዊት ከመገንባት በተጓዳኝ ዘመኑን የዋጁ ወታደራዊ ቴክኖሎጂዎች እየፈጠረ እንደሚገኝ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ብርጋዴር ጀነራል ከበደ ረጋሳ ገለጹ። ዩኒቨርሲቲው በምህንድስና፣ በጤና ሳይንስ፣ በቢዝነስ፣ በኃብት አስተዳደር እና በሌሎች የትምህርት መርኃ ግብሮች በመጀመሪያ፣ በሁለተኛ እና በሶስተኛ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች ዛሬ አስመርቋል።   በምረቃ መርኃ ግብሩ የመከላከያ ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሐመድ፣ የመስኖና ቆላማ አካባቢዎች ሚኒስትር አብርሃም በላይ(ዶ/ር)፣ የጤና ሚኒስትር ዴኤታ እና የዩኒቨርሲቲው ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ዶክተር ደረጀ ዱጉማ፣ የመከላከያ ከፍተኛ መኮንኖች፣ የተለያዩ ሀገራት ወታደራዊ አታሼዎችና የተመራቂ ቤተሰቦች ተገኝተዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ብርጋዴር ጄኔራል ከበደ ረጋሳ፤ ዩኒቨርሲቲው በተለያዩ የትምህርት መስኮች ወታደራዊ፣ ሲቪል እና የጎረቤት ሀገራት ተማሪዎችን በማሰልጠን ላይ ይገኛል ብለዋል። በዚህም ዩኒቨርሲቲው በእውቀትና በክህሎት ብቁ የሆነ የሰው ኃይል እያፈራ መሆኑንም ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲው የመከላከያ ሰራዊቱን የተልዕኮ አፈጻጸም ወደ ላቀ ደረጃ የሚያደርሱ ወታደራዊና ሲቪል አመራሮችን በማፍራት ላይ እንደሚገኝም ገልጸዋል።   በቴክኖሎጂው ዘርፍ ሀገርን የሚያሻግሩ ሥራዎች በመስራት ላይ እንደሚገኝ ጠቁመው የመከላከያን የሰለጠነ የሰራዊት ግንባታ በማገዝ ላይ መሆኑንም ተናግረዋል። ዩኒቨርሲቲው የሰራዊቱን ስምና ዝና በሚመጥን መልኩ የተዋቀረ ሲሆን ከመማር ማስተማር ስራዎች በተጓዳኝ የተለያዩ የጥናትና ምርምር ስራዎችና ሌሎች ህብረተሰቡን የሚጠቅሙ ተግባራት እየሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ ዘመናዊ ሰራዊት ለመገንባት ከውጭ የምታስገባቸውን ቴክኖሎጂዎች በሀገር ውስጥ ለመተካት ዩኒቨርሲቲው የተለያዩ ስራዎችን በመሥራት ላይ መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል። ተመራቂዎች ባገኙት እውቀትና ከፍተኛ ክህሎት ሀገራቸውን በብቃት ማገልገል እንደሚገባቸው መልዕክት አስተላልፈዋል። የኢትዮጵያ መከላከያ ዩኒቨርሲቲ በ2025 ከአፍሪካ አምስት ምርጥ የመከላከያ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ የመሆን ራዕይ ሰንቋል።
የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ አሰራሩን በቴክኖሎጂ ለማስደገፍ የጀመራቸውን ተግባራት አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል - ቋሚ ኮሚቴው
Jul 11, 2025 202
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ አሰራሩን በቴክኖሎጂ ለማስደገፍ የጀመራቸውን ተግባራት አጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። ቋሚ ኮሚቴው በተሻሻለው የኢትዮጵያ ምርጫ፤ የፖለቲካ ፓርቲዎች ምዝገባና የምርጫ ሥነ ምግባር ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ የውይይት መድረክ አካሂዷል። በውይይት መድረኩ የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችና ማህበራት፣ መገናኛ ብዙሃን ኃላፊዎችን ጨምሮ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል። አዋጁ በምርጫ ጣቢያ ደረጃ የሚቀርብ ማንኛውም ቅሬታ በምርጫ ጣቢያ ኃላፊ ታይቶ ውሳኔ እንዲሰጥበት የሚደነግግ ሲሆን የምርጫ ክልል አቤቱታ ሰሚ ኮሚቴ አባላት ከዚህ በፊት ከህብረተሰቡ ይመደብ የነበረው ቀርቶ ቦርዱ አሰልጥኖ በሚመድባቸው የምርጫ አስፈጻሚዎች እንዲተኩ የሚያደርግ ነው። ከዚህ ቀደም በነበረው አዋጅ አንድ ፓርቲ ሀገራዊ ፓርቲ ሆኖ ለመመዝገብ የሚመለምለው አባል ከ5 ክልሎች የነበረ ሲሆን በተሻሻለው አዋጅ አንድ ፓርቲ አባላትን መመልመል ያለበት ከ7 ክልሎች ሊሆን እንደሚገባም በአዋጁ ተመላክቷል። አንድ ፓርቲ ከመንግሥት ድጋፍ ለማግኘት ከ30 በመቶ ከሚሆነው አባሉ የአባልነት መዋጮ መሰብሰብ እንደቅደመ ሁኔታም ተቀምጧል። በአዋጁ መሰረት ጥሰት ፈጽመው የተገኙ ፓርቲዎች እስከ አምስት ዓመት ድረስ ሊታገዱ የሚችሉበት ድንጋጌም ከተካተቱ ጉዳዮች መካከል ነው። በውይይቱ ከተሳተፉ መካከል የቦሮ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ተወካይ መብራቱ ዓለሙ(ዶ/ር) በሰጡት አስተያየት፤ በምርጫ ጣቢያ ለሚቀርቡ ጥያቄዎች የምርጫ ጣቢያ ኃላፊ አይቶ ውሳኔ ይሰጣል የሚለው የአንቀጹ ክፍል ለአተገባበር አስቸጋሪ ሊሆን ይችላል ብለዋል።   የቁጫ ሕዝብ ዲሞክራሲያዊ ፓርቲ ተወካይ ባንዲራ በላቸው እንደገለጹት፤ ፓርቲዎች 30 በመቶ መዋጮ እንዲያሰባስቡ የተቀመጠው ድንጋጌ ከነባራዊ ሁኔታ አኳያ ተግባራዊ ሊሆን ይችላል ወይ የሚለው ሊጤን እንደሚገባ ተናግረዋል።   የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማህበራት ፌደሬሽን ዋና ዳይሬክተር አባይነህ ጉጆ በበኩላቸው በአዋጁ የአካል ጉዳተኞችን ተሳትፎ የሚያጎለብቱ ድንጋጌዎች ሊካተቱ ይገባል ብለዋል።   የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ሜላተወርቅ ኃይሌ በሰጡት ማብራሪያ በአዋጁ ፓርቲዎች 30 በመቶ ያህል መዋጮ ከአባላት ሊሰበሰቡ እንደሚገባ የተደነገገው ፓርቲዎች በመንግሥት በጀት ላይ ብቻ እንዳይመሰረቱና ራሳቸውን እንዲችሉ ለማድረግ ነው ብለዋል። አዋጁ አካል ጉዳተኞችንና ሴቶችን አካታች በሆነና ተሳትፏቸውን በሚያሳድግ መልኩ መቃኘቱን አንስተዋል። የመንግሥት ሰራተኞች በምርጫ ውድድር ወቅት ደሞዛቸውን ይዘው እንዲሳተፉ መደረጉ ለፖለቲካ ምህዳሩ ትልቅ እርምጃ መሆኑን አብራርተዋል።   የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ ተስፋዬ ነዋይ በሰጡት ማብራሪያ፤ በምርጫ ጣቢያ ደረጃ የሚነሱ ቅሬታዎች በምርጫ ጣቢያ ኃላፊ እንዲፈታ አቅጣጫ የተቀመጠው ፈጣን ምላሽ ለመስጠት ታልሞ መሆኑን አስረድተዋል። እንዲያም ሆኖ ቅሬታዬ አልተፈታም የሚል ማንኛውም አካል ጥያቄውን በየደረጃው የሚያቀርብበት አሰራር መዘርጋቱን ጠቁመዋል።   በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ አዝመራ አንደሞ በበኩላቸው በህዝባዊ የውይይት መድረኩ የተነሱ ሀሳቦች ለአዋጁ ውሳኔ ሀሳብ የሚረዱ ግበዓቶች የተገኙበት ነው ብለዋል። በቀጣይም ሀገራዊ ምክክር ላይ የፓርቲዎች ተሳትፎ ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም አመልክተዋል። በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እውነቱ አለነ በበኩላቸው ፓርቲዎች የወጣቶችን፣ የአካል ጉዳተኞችንና የሴቶችን ተሳትፎ ለማሳደግ የበለጠ ሊሰሩ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአባልነት መዋጮን በተመለከተም ፓርቲዎች አባላቶቻቸውን ሊያበረታቱ እንደሚገባም ነው የተናገሩት። የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ቴክኖሎጂን ስራ ላይ ለማዋል የጀመራቸውን ተግባራት ሊያጠናክር እንደሚገባ ጠቁመው ፓርቲዎችም ይሄንኑ ስራ ሊደግፉ እንደሚገባ አመልክተዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም