ቀጥታ፡
ፖለቲካ
በመግባባት መንፈስ እየመከርን ነው - የዋናው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ተመካካሪዎች
Jul 21, 2026 122
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ)፦ በመግባባት መንፈስ እየመከሩ እንደሚገኝ የዋናው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ተመካካሪዎች አስታወቁ። ምክክሩ የዘመናት ጥያቄዎችን መልስ እንደሚያስገኝ እምነታቸው መሆኑን ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በሀገር ውስጥና በውጭ ያሉ ኢትዮጵያውያንን በማሳተፍ ምክክር የሚደረግባቸውን ስምንት አጀንዳዎች መለየቱ ይታወሳል። በአጀንዳዎቹ ላይ አራት ሺህ ተመካካሪዎች በተገኙበት በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ምክክር እየተደረገባቸው ይገኛል። ከተመካካሪዎቹ መካከል አቶ ቀጄላ መርዳሳ እንዳሉት፤ ኮሚሽኑ ምክክሩ አካታች በሆነ መንገድ ተመካካሪዎቹን መምረጡን በአካል በመሳተፍ አረጋግጠዋል። በምክክሩም ሕዝብ የተሳተፈበት መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የምክክሩ ሌላው ጠንካራ ጎን መሆኑን አመልክተዋል። ምክክሩ በኢትዮጵያውያን ተወጥኖ በራሳቸው መፍትሔ የሚበጅለት መሆኑ ከሌሎች ሀገራት ልዩ ያደርገዋል ያሉት አቶ ቀጄላ፤ የኢትዮጵያ የምክክር ሂደት ለሌሎች ሀገራትም አርዓያ የሚሆን ነው ብለዋል።   አርክቴክት ዮሐንስ መኮንን በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ ምክክር እንዲደረግ ሊቃውንት፣ የሀገር ሽማግሌዎችና የሀገር ጉዳይ ያገባኛል የሚሉ ዜጎች ለዘመናት ሲጠይቁት የነበረ ጉዳይ መሆኑን አስታውሰዋል። አሁን የጀመርነው ሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ለዚያ ጥያቄ መልስ የሰጠ ነው ያሉት አርክቴክት ዮሐንስ፤ ሁሉም በጋራ ሆኖ ልዩነቱን ተመካክሮ መፍትሔ የሚያበጅበት ትልቅ የታሪክ ምዕራፍ ተከፍቷል ብለዋል። ምክክሩ ተስፋ ሰጪ መሆኑን ጠቅሰው፤ ወደፊት ልዩነቶችን ለመፍታት ኃይል ሳይሆን የሰለጠነ አካሄድ እንዲሆን መሠረት የሚጥል ነው ብለዋል።   ሌላኛው ተመካካሪ ወጣት አርአያም ጽጌ በሰጠው አስተያየት፤ ምክክር የጋራ መግባባትን መፍጠር የሚያስችል መሆኑን ገልጿል። ምክክሩ አለመግባባቶችን ለመፍታት ምቹ መድረክ የሚፈጠርበት መሆኑን ጠቅሶ፤ ሂደቱ በመከባበር፣ በመተባበርና በመግባባት መንፈስ እየተሳተፍንበት ነው ብሏል።   ሌላው የምክክሩ ተሳታፊ ቶፊቅ ሀጫሉ (ዶ/ር) እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም ምክክር ባለመደረጉ በመግባባት የሚፈቱ ጉዳዮች ዋጋ ማስከፈላቸውን ገልጸዋል። መሰል ችግሮችን ለማስወገድ ምክክሩ ትልቅ ዕድል ይዞ መምጣቱን ገልጸው፤ በምክክሩ ላይም አሳታፊና ያለገደብ ሐሳብ እየሰጠን ነው ብለዋል።   ሌላኛው ተመካካሪ ባንዲራ በላቸው በበኩላቸው፤ ለችግሮች ዘላቂ መፍትሔዎችን ማመላከት የሚያስችሉ ምክረ ሐሳቦች እንዲፈልቁ በቂ ዝግጅት መደረጉን ተመልክቻለሁ ብለዋል።  
በሀገራዊ የምክክር ጉባኤው ሂደት መግባባትን የሚፈጥር ግልፅና ተስፋ ሰጪ ምክክር እያደረግን ነው
Jul 21, 2026 109
አዲስ አበባ፤ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ)፦ በሀገራዊ የምክክር ጉባኤው ሂደት ጠንካራ መግባባትን የሚፈጥር ግልፅና ተስፋ ሰጪ ምክክር እያደረግን ነው ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው ተመካካሪዎች ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት ዋናው የምክክር ጉባኤ በአዲስ አበባ አዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል አራት ሺህ የሕዝብ ወኪል ተመካካሪዎች በተገኙበት በይፋ ተጀምሯል። በሁሉም ክልሎች፣ በሁለቱ ከተማ አስተዳደሮችና በውጭ ከሚኖሩ ዜጎች ሕዝብ የወከላቸው ተመካካሪዎችም ከትናንት ሐምሌ 13 ቀን 2018 ዓ.ም ጀምሮ በንዑስ ቡድኖች በመከፋፈል በተመደቡበት አጀንዳ ላይ መመካከር ጀምረዋል። የምክክሩ ሂደት ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍሎች ያሳተፈና በግልጽነት መርህ ላይ በተመሠረተ መልኩ እየተካሄደ ሲሆን፤ ለብዝኃነት ዕውቅና በመስጠት በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ አለው። በእያንዳንዱ ንዑስ ቡድን ውስጥ 50 ተመካካሪዎች የሚገኙ ሲሆን፣ በአጠቃላይ 80 አነስተኛ ቡድኖች በተመደቡላቸው አጀንዳዎች ላይ እየመከሩ ይገኛሉ። በአንድ አጀንዳ ላይ እንዲመክር 500 ተመካካሪዎችን በሥሩ የያዘ ዐቢይ ቡድን፣ እያንዳንዳቸው 50 ተመካካሪዎችን የያዙ 10 የሚሆኑ ንዑስ ቡድኖችን በመያዝ ተዋቅሯል። በሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ላይ ከመላው ሀገሪቷ የተውጣጡ የማኅበረሰብ ክፍሎች ኮሚሽኑ ለምክክሩ በመረጣቸው ስምንት ዋና ዋና አጀንዳዎች ዙሪያ በመመካከር ላይ ናቸው። አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ተመካካሪዎች እንዳሉትም፤ በዋናው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ላይ ግልጽና ተስፋ ሰጪ ሂደት ላይ ምክክር እያደረጉ ነው። የሀገራዊ ምክክሩ ዋና ጉባኤ የመደማመጥና የጋራ መግባባት ባህልን በማጠናከር የተሻለች ኢትዮጵያን ለመገንባት ትልቅ ዕድል መሆኑን ገልጸዋል።   ከተመካካሪዎች መካከል ሲሳይ ዘለቀ፤ የምክክር መድረኩ የሀገሪቱን የጋራ የወደፊት ዕድል ለመወሰን ትልቅ ተስፋ የተጣለበት መሆኑን ገልጸዋል። ሁሉም ተመካካሪዎች ለሀገር ይበጃል ያለውን ሐሳብ በማዋጣት በግልጽነት እየተመካከረ እንደሚገኝ ተናግረው፤ እስካሁን ያለው ሂደት ፍጹም ግልጽና ተስፋ በተሞላበት መልኩ እየተካሄደ መሆኑን ጠቁመዋል።   ሌላኛው ተመካካሪ መምህር ሞገስ ፍሥሓ በበኩላቸው፤ በመጀመሪያ ደረጃ የምክክር መድረኩ እርስ በእርስ እንድንተዋወቅ ዕድል ፈጥሮልናል ብለዋል። ሂደቱ በጣም ደስ በሚል ሁኔታ እየሄደ መሆኑን ጠቁመው፤ መድረኩ ተመካክረንና ተወያይተን አዲሷን ኢትዮጵያ እውን ለማድረግ ትልቅ ዕድል የፈጠረ መሆኑን ገልጸዋል። ምክክር አንዱ የሌላውን ሐሳብ በማዳመጥ መግባባት መፍጠር ነው ያሉት ሌላኛው ተመካካሪ ናስር አብደላ፤ በምክክር ጉባኤውም ሁሉም ተመካካሪ ሐሳቡን በነፃነት እየገለጸና እየመከረ ነው ብለዋል።   የምክክሩን አሁናዊ ሂደት በማድነቅ፣ ሂደቱ ከመከራከር ይልቅ የመደማመጥና የመመካከር ባህልን የሚከተል መሆኑን ገልጸዋል።
"ትልልቅ ውሳኔዎች ከትንንሽ የውይይት ጠረጴዛዎች ይጀምራሉ!"
Jul 21, 2026 152
የኢትዮጵያ ሃገራዊ ምክክር ኮሚሽን ሀምሌ 14/2018 ዓ.ም በሀገራዊ ምክክር ጉባኤ የንዑስ ቡድን ውይይቶች ልዩነቶች የሚደመጡበት፣ ሐሳቦች የሚፈተኑበት፣ ጥያቄዎች በጥልቀት የሚመረመሩበት እና መግባባት በትዕግሥት የሚገነባበት ወሳኝ መድረክ ነው። እያንዳንዱ ተሳታፊ ድምፁን በነፃነት ያሰማል፤ የሌሎችን ሀሳብ በአክብሮት ያዳምጣል፤ የተለያዩ እይታዎችም በምክንያትና በማስረጃ ይመዘናሉ። በዚህ ሂደት የሚፈጠረው መግባባት ለጋራ ራዕይ መገንባት እና ለዘላቂ ሰላም ጠንካራ መሠረት ይሆናል። እዚህ ላይ የሚቀርብ እያንዳንዱ ሀሳብ ዋጋ አለው፤ እያንዳንዱ ድምፅ ይደመጣል፤ እያንዳንዱ ውይይት የጋራ ነገን ለመገንባት አንድ ተጨማሪ እርምጃ ነው።   በሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ውስጥ የንዑስ ቡድን ውይይቶች ከመደበኛ ውይይት በላይ የሆነ ትርጉም አላቸው። እነዚህ መድረኮች የተለያዩ ልምዶች፣ እይታዎች፣ እሴቶች እና ተሞክሮዎች በአንድ ጠረጴዛ ዙሪያ ተሰባስበው በጥልቀት የሚመክሩባቸው ወሳኝ የሀሳብ መፍጫ ማዕከላት ናቸው። በእነዚህ ውይይቶች ውስጥ እያንዳንዱ ተሳታፊ ሀሳቡን በነፃነትና በኃላፊነት ያቀርባል። የሌሎችን ሀሳብ በትዕግሥት ያዳምጣል፣ ጥያቄዎችን ያነሳል፣ ማብራሪያዎችን ይጠይቃል፣ እንዲሁም በማስረጃና በምክንያት የተደገፉ አስተያየቶችን ያቀርባል። ይህ ሂደት ልዩነቶችን እንደ ግጭት ሳይሆን እንደ የመማማሪያና የመግባቢያ ዕድል እንዲታዩ ያግዛል። ተመካካሪዎች ሀሳቦችን በአንድ ጊዜ አያፀድቁም። ይወያዩባቸዋል፣ ይመረምራሉ፣ ይሻሻላሉ፣ ይጠናከራሉ። በዚህም የተለያዩ እይታዎችን ያካተቱና ሰፊ ድጋፍ ሊያገኙ የሚችሉ ምክረ ሀሳቦች ይፈጠራሉ። የንዑስ ቡድን ውይይቶች አስፈላጊነታቸው በሐሳብ ልውውጥ ብቻ አይወሰንም። እርስ በርስ የመተማመን ባሕልን፣ የመደማመጥ ልምድን እና የጋራ መፍትሔ ፍለጋን ያጠናክራሉ። ሀገራዊ ጉዳዮች በአንድ ወገን እይታ ብቻ ሳይሆን ከተለያዩ አቅጣጫዎች ሲታዩ የተሻሉ መፍትሔዎች ሊገኙ እንደሚችሉ ይህ ሂደት ያሳያል።   በመጨረሻም የንዑስ ቡድን ውይይቶች የሀገራዊ ምክክር ልብ ናቸው። እዚህ የሚነሳ ሀሳብ የነገን አቅጣጫ ሊቀይር ይችላል። እዚህ የሚፈጠር መግባባት የጋራ የወደፊት ጉዞን ሊያጠናክር ይችላል። የተለያዩ ድምፆች በአንድ መድረክ ተደምጠው ወደ ጋራ መፍትሔ ሲደርሱ፤ የሀገራዊ ምክክር እውነተኛ ዓላማ በተግባር ይገለጣል። ሀገራዊ ምክክር ልዩነቶችን በውይይት የሚያቀራርብ፣ የጋራ መግባባትን የሚያጠናክር ሀገራዊ ጉዞ ነው።  
ኢትዮጵያን በዘላቂነት ለማጽናትና ጽኑ መሠረት ላይ ለመገንባት በሚያስችሉ አጀንዳዎች ላይ ምክክር እያደረግን እንገኛለን
Jul 21, 2026 112
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ) ፦ኢትዮጵያን በዘላቂነት ለማጽናትና ጽኑ መሠረት ላይ ለመገንባት በሚያስችሉ አጀንዳዎች በሠለጠነ መንገድ ምክክር እያደረግን እንገኛለን ሲሉ ተመካካሪዎች ገለጹ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ተመካካሪዎች ከትናንት ጀምሮ በንዑስ ቡድኖች በመከፋፈል በተመደቡበት አጀንዳ ላይ መመካከር ጀምረዋል፡፡ የምክክሩ ሂደት ሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍሎች ያሳተፈና በግልጽነት መርህ ላይ በተመሠረተ መልኩ እየተካሄደ ሲሆን፤ ለብዝሃነት ዕውቅና በመስጠት በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ አለው። በእያንዳንዱ ንዑስ ቡድን ውስጥ 50 ተመካካሪዎች ሲገኙ፤ በአጠቃላይ 80 አነስተኛ ቡድኖች በተመደቡላቸው አጀንዳዎች ላይ እየመከሩ ናቸው። በአንድ አጀንዳ ላይ እንዲመክር 500 ተመካካሪዎችን በሥሩ የያዘ ዐቢይ ቡድን፣ እያንዳንዳቸው 50 ተመካካሪዎችን የያዙ 10 የሚሆኑ ንዑስ ቡድኖችን በመያዝ ተዋቅሯል። በሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ላይ ከመላው ሀገሪቱ የተውጣጡ የማኅበረሰብ ክፍሎች ኮሚሽኑ ለምክክሩ በመረጣቸው ስምንት ዋና ዋና አጀንዳዎች ዙሪያ በመመካከር ላይ ናቸው። የምክክር ጉባኤው ተመካካሪ ሻምበል አለማየሁ ታፈሰ እንደገለጹት፤ በአንድ ሀገር የሚገኙ ዜጎች በማያግባቡ ጉዳዮች ላይ በምክክር የጋራ መግባባት መፍጠር ለሀገራዊ አንድነት ፋየዳው የላቀ ነው። ለዚህም እኛ ኢትዮጵያውያን ለዘመናት ስር በሰደዱ ጉዳዮች ዙሪያ በሰከነና በሰለጠነ መንገድ በመመካከር ሀገራዊ መግባባት ለመፍጠር እየመከርን ነው ብለዋል። የተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች የሚያነሱትን ሐሳብ በማዳመጥና የራሳቸውን ሐሳብ በማካፈል ለሀገር ይበጃል የሚል ምክረ ሃሳብ ለማቅረብ በሰለጠነ መንገድ እየተመካከሩ መሆናቸውን አክለዋል።   ተመካካሪ ዝማማ አቡሃይ በበኩላቸው፤ በምክክሩ ሀገርን የሚያሻግር መፍትሔ እንድናመጣ ሀገርና ሕዝብ አደራ ጥሎብናል ብለዋል። ተመካካሪዎችም ይህንን ታሪካዊ አደራ በብቃት ለመወጣት ሙሉ ዝግጁ መሆናቸውን ጠቅሰዋል፡፡ የምክክሩ ሂደት ሁሉንም ያካተተ መሆኑ የተለያዩ ዕይታዎችና ሃሳቦች በነፃነት እንዲንሸራሸሩ እንዲሁም የኢትዮጵያን ብዝሃነት የጠበቀ ውይይት እንዲደረግ ትልቅ አቅም ፈጥሯል ሲሉ ገልጸዋል። ተመካካሪ ሊዲያ ተስፋዬ በበኩላቸው፣ በምንመካከርባቸው አጀንዳዎች ላይ ሐሳባችንን በነፃነት በማቅረብ ለኢትዮጵያ ይጠቅማል ብለን ያሰብነውን መፍትሔ ለማምጣት እየተጋን ነው ብለዋል፡፡   በምክክሩ ሂደት ባለቸው ተሳትፎም የራሳቸውን ሐሳብ ከማካፈል ባለፈ፣ ከሌሎች ተመካካሪዎች የሚነሱ ሃሳቦችን በመስማት ጥሩ የምክክር ጊዜ እያሳለፉ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ በጉባኤው ላይ ከተለያዩ አጀንዳዎች መመካከር ባለፈ ከተለያየ አካባቢ የመጡ ዜጎች እርስ በእርስ በደንብ እንዲተዋወቁ እንዳገዛቸው ገልጸዋል። አራት ሺህ ተመካካሪዎች እየተሳተፉበት የሚገኘው የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም መጀመሩ ይታወቃል።    
ኢትዮጵያ በቀጣናው ሽብርተኝነትን በመመከት ረገድ የማይተካ ሚናዋን እየተወጣች ነው-አምባሳደር ሃደራ አበራ
Jul 21, 2026 154
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በቀጣናው ሽብርተኝነትን በመከላከል ረገድ ግንባር ቀደም ሚናዋን እየተወጣች እንደምትገኝ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሃደራ አበራ ገለጹ። የአፍሪካ ህብረት የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት 1354ኛ የሚኒስትሮች ስብሰባውን ዛሬ በበይነ መረብ አካሂዷል።   ስብሰባው በአፍሪካ ሽብርተኝነትና በዓመፅ የታጀበ ጽንፈኝነትን መከላከል በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ያተኮረ ነው። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሃደራ አበራ በስብሰባው ላይ ተሳትፈዋል። አምባሳደር ሃደራ አበራ ዓለም አቀፍ የሽብርተኛ ቡድኖች በአፍሪካ ሰላምና ደህንነት የደቀኑትን ስጋት አንስተዋል። የሽብርተኛ ቡድኖች ዲጂታል አማራጮች እና ማህበራዊ ሚዲያ ጨምሮ ቴክኖሎጂዎችን አባላትን ለመመልመል፣ ፕሮፓጋንዳ ለማሰራጨት እና ጽንፈኝነትን ለማስፋፋት እየተጠቀሙበት እንደሚገኝ አመልክተዋል።   ዓለም ላይ ያሉ ለውጦችን ከግምት ውስጥ በማስገባት የአፍሪካ ተጠባባቂ ኃይልን ወደ ስራ ማስገባት እና የአፍሪካ ሀገራት በደህንነት እና አስተዳደር ያላቸውን ትብብር ማጠናከር የሚያስችሉ አህጉራዊ የአሰራር ማዕቀፎችን በሚገባ መተግበር እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። አምባሳደር ሃደራ ኢትዮጵያ የሀገር ውስጥ ሽብርተኝነትን ለመከላከል እና በቀጣናው ያለውን የሽብርተኝነት ነቀርሳ ለማስወገድ እያደረገች ያለውን የማይተካከል አስተዋጽኦ ማንሳታቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል።
ኢትዮጵያ እየመከረች ነው!
Jul 21, 2026 164
የሐምሌ 14 ቀን 2018 ዓ.ም የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ዐበይት መረጃዎች በትናንትናው ዕለት በቡድን ተከፋፍለው መመካከር የጀመሩት ተመካካሪዎች ዛሬም በየቡድናቸው በመሆን መመካከር ቀጥለዋል፡፡ 50 ተመካካሪዎችን በመያዝ በ80 ቡድን ተከፋፍለው መመካከር የጀመሩት ንዑሳን ቡድኖች በተሟላ ሁኔታ ከትላንት ከሰዓት ጀምሮ በየንዑስ ቡድናቸው አስር አስር በመሆን ምክክር በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይህ ሂደት እስከ ነገ የሚቀጥል ይሆናል፡፡ በዚህ ሂደት ተመካካሪዎች በሚመካከሩባቸው የአጀንዳ ሃሳቦች ላይ በርካታ ሃሳቦችን እና ምልከታዎችን በማቅረብ ላይ ይገኛሉ፡፡ሂደቱ ተመካካሪዎች ላለመግባባት መንስኤ የሆኑ እጅግ መሰረታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ያሉ አመለካከቶችን እና ምክንያቶችን ከስር መሰረቱ አንዳቸው ሌላቸውን እንዲረዱ መደላድል እንደሚፈጥር ይጠበቃል፡፡ ይህንን ሂደት ለማሳካት የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከተለያዩ ተቋማት በሙያቸው፣ በትምህርት ዝግጅታቸው እና ለአጀንዳ ሃሳቦቹ ባላቸው ሙያዊ ቅርበት ብቁ ናቸው ብሎ ያመነባቸው 80 የሚጠጉ የባለሙያዎች ስብስብ (Panel of Experts) በማሰባሰብ በሀገራዊ ምክክር ጉባኤው ላይ እያሳተፈ ይገኛል፡፡   የባለሙያዎች ስብስብ በአጀንዳ ነጥቦች ላይ ለሚፈጠሩ ብዥታዎች ማብራሪያ በመስጠት ሂደቱን በመደገፍ ላይ ይገኛሉ፡፡ በሌላ በኩል በዚህ የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ የተለያዩ የሀገር ውስጥ ተቋማት ሂደቱን ለመታዘብ ለኮሚሽኑ ጥያቄ ባቀረቡት መሰረት ከኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ጥምረት፣ ከተለያዩ የሙያ ማህበራት፣ ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባኤ እና ከኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን የተውጣጡ ከ50 በላይ ገለልተኛ ታዛቢዎች የምክክር ሂደቱን እየታዘቡ ይገኛሉ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ሐምሌ 14 ቀን 2018 ዓ.ም
ልማትና ዴሞክራሲን ጎን ለጎን በማስኬድ ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ በተሰሩ ዘርፈ ብዙ ተግባራት የላቀ ውጤት ተመዝግቧል
Jul 21, 2026 214
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 14/2018 (ኢዜአ)፦ ልማትና ዴሞክራሲን ጎን ለጎን በማስኬድ ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ በተሰሩ ዘርፈ ብዙ ተግባራት የላቀ ውጤት ተመዝግቧል ሲሉ የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት እና የዋና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አደም ፋራህ ገለጹ። የብልፅግና ፓርቲ የብሔራዊነት ገዥ ትርክትን ማስረጽና ተቋማዊ አቅምን በማጠናከር ላይ ትኩረት አድርጎ እንደሚሰራም አቶ አደም ፋራህ ተናግረዋል። የብልፅግና ፓርቲ የ2018 በጀት ዓመት አፈጻጸም ግምገማና የ2019 በጀት ዓመት መሪ ዕቅድ የውይይት መድረክ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል።   የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት እና የዋና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አደም ፋራህን ጨምሮ የዋና ጽህፈት ቤት የዘርፍ ኃላፊ ሚኒስትሮች፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ የቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊዎችና ሌሎች አመራሮች እየተሳተፉ ናቸው። አቶ አደም ፋራህ በመድረኩ እንደገለፁት ልማትና ዴሞክራሲን ጎን ለጎን በማስኬድ ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ በተሰሩ ዘርፈ ብዙ ተግባራት የላቀ ውጤት ተመዝግቧል ብለዋል። የ2018 በጀት ዓመት በተቋም ግንባታ፣ በዴሞክራሲ ሥርዓት እና በልማት ሥራዎች ጉልህ ውጤቶች የተመዘገቡበት ዓመት ነው ሲሉም ገልጸዋል። በጀት ዓመቱ ከፓርቲ ግንባታ አኳያ ብልፅግና በአደረጃጀት፣ በአሰራር፣ በሰብዓዊና ቁሳዊ ሀብት እንዲሁም በማስፈጸም አቅሙ ተጠናክሮ የወጣበት ዓመት መሆኑንም ጨምረው ተናግረዋል። በተጨማሪም ድርብርብ ተልዕኮዎችን በታቀደው መሰረት ማሳካት የተቻለበት በጀት ዓመት ነው ብለዋል። መላው ህዝብ በእያንዳንዱ ተልዕኮ ላይ በንቃት እንዲሳተፍ በመደረጉና በባለቤትነት ስሜት ከብልፅግና ፓርቲ ጎን በመቆሙ፣ ለዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ጠንካራ መሰረት የጣለውን 7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ መንታ ግቦች በላቀ አፈጻጸም ማሳካት ተችሏል ነው ያሉት።   ልማትና ዴሞክራሲን ጎን ለጎን በማስኬድ ሁለንተናዊ ብልፅግናን ለማረጋገጥ በተከናወኑ ዘርፈ-ብዙ ተግባራት የላቀ ውጤት መመዝገቡንም ገልጸዋል። አክለውም የፓርቲውን ግዙፍ አቅም አሟጦ በመጠቀምና የአመራር ሥነ-ምግባር ልህቀትን በማረጋገጥ የሕዝብን ሁለንተናዊ ብልፅግና እውን ለማድረግ መትጋት እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የአመራርና አባላትን ጥራት ማረጋገጥ፣ የብሔራዊነት ገዥ ትርክትን ማስረፅ እና የፓርቲውን ተቋማዊ የማዕቀፍ ስታንዳርድ (Standardization) የመገንባት ሥራ በተጠናከረ መንገድ እንደሚከናወን ተናግረዋል። ለዚህም የአመራሩ፣ የአባላቱና የመላው ሕዝብ ርብርብ እጅግ አስፈላጊ መሆኑን አመልክተዋል። ለሁለት ተከታታይ ቀናት በሚቆየው በዚህ መድረክ፤ በ2018 ዓ.ም የአፈጻጸም ሪፖርት እና በ2019 ዓ.ም መሪ ዕቅድ ላይ ውይይት የሚደረግ ሲሆን፣ የቀጣይ አቅጣጫዎችም ይቀመጣሉ ተብሎ ይጠበቃል።
እየተካሄደ የሚገኘው ሀገራዊ ምክክር በኢትዮጵያ ብሔራዊ መግባባት ለመፍጠር ትልቅ ድርሻ አለው
Jul 21, 2026 195
ሆሳዕና፤ ሐምሌ 14/2018(ኢዜአ)፦ እየተካሄደ የሚገኘው ሀገራዊ ምክክር ለኢትዮጵያ የቆዩ ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ የሚያመጣና ብሔራዊ መግባባት ለመፍጠር ትልቅ ድርሻ እንዳለው በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የሚሰሩ ምሁራን ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ከህዝብ የሰበሰባቸውን አጀንዳዎች ለይቶ እና አደራጅቶ ለምክክሩ ይፋ ባደረጋቸው አጀንዳዎች ላይ ምክክር እየተካሄደ ይገኛል። የምክክር ሂደቱ የኢትዮጵያን የቆዩ ስብራቶች በማከም የጸናችና ለትውልዱ የምትመች ሀገር ለመገንባት ጠንካራ መሰረት ለማኖር ያስችላል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፤ ሐምሌ 8/2018 ዓም በምክክር ጉባኤው መክፈቻ ላይ እንደተናገሩት በምክክሩ ከየሰፈራችን ወጥተን ለኢትዮጵያ ስንመክር፣ ለልጆቻችን ስንልና እነርሱን እያሰብን ስንወያይ ውጤቱ ፍሬያማ ይሆናል ማለታቸው ይታወቃል። በጉዳዩ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው በዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ የሚሰሩ ምሁራን እንዳሉት እየተካሄደ የሚገኘው ሀገራዊ ምክክር ልዩነቶችን በውይይት በመፍታት ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለው። በዩኒቨርሲቲው የሰላምና ደህንነት ጥናት መምህርና ተመራማሪ ተመስገን ቶማስ (ዶ/ር) አሁን እየተካሄደ የሚገኘው ሀገራዊ ምክክር አለመግባባቶችን በውይይት በመፍታት ለጋራ ተጠቃሚነት ትልቅ እገዛ ያደርጋል ብለዋል። የሀገር እድገትና ዘላቂ ሰላም መረጋገጥ የዜጎችን የነቃ ተሳትፎ እንደሚጠይቅ ጠቁመው ጎታች አመለካከቶችን በሀገራዊ ምክክሩ በመፍታት ለጋራ ተጠቃሚነት መስራት ይገባል ነው ያሉት። ችግሮችን በጠረጴዛ ዙሪያ መምከር ለቆዩ ችግሮች የጋራ መፍትሔ ማምጣትና የተዛቡ ትርክቶችን ማረም እንደሚያስችልም ነው የተናገሩት። እየተካሔደ ያለውን ሀገራዊ ምክክር በአግባቡ በመጠቀም ለሀገር እድገትና ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ መጠቀም ይገባል ብለዋል። የምክክር ሂደቱ ለቆዩ ችግሮች ዘላቂ መፍትሄን ይዞ ከመምጣቱ ባለፈ የህዝቦችን አብሮነት በማጠናከር የኢትዮጵያን የማንሰራራት ጉዞ የሚያጠናክር ነው ያሉት ደግሞ በዩኒቨርሲቲው የፖለቲካ ሳይንስ መምህሩ አበራ ሄቢሶ ናቸው። ለዚህም በኮሚሽኑ ተለይተው የቀረቡ አጀንዳዎች ለቆዩ ችግሮች ዘላቂ መፍትሄ ለመስጠትና ለተተኪው ትውልድ የተሻለች ሀገር ለማስተላለፍ ተጨማሪ አቅም ይፈጥራል ሲሉ ገልጸዋል። የሚነሱ ችግሮችን በማረም ለሀገረ መንግስት ግንባታው መጠናከር የሚያበረክተው አስተዋጽኦም ከፍተኛ መሆኑን ነው የተናገሩት።
ኢትዮጵያ በልማት እንቅስቃሴዎችና በውጭ ግንኙነት መስክ ተጨባጭ ውጤቶችን እያስመዘገበች ትገኛለች
Jul 20, 2026 766
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በልማት እንቅስቃሴዎችና በውጭ ግንኙነት መስክ ያስመዘገበቻቸው ውጤቶች የሀገሪቱን ሁለተናዊ ብልፅግና ከማረጋገጥ ባለፈ የውሳኔ ሉዓላዊነትን በተግባር ያረጋገጡ መሆናቸውን ምሁራን ገለጹ፡፡ በኢትዮጵያ ፐብሊክ ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የዲፕሎማሲና ዓለምአቀፍ ግንኙነት መምህር እንዳለ ንጉሤ እንደገለጹት፤ በፖለቲካ ሳይንስና ዲፕሎማሲ መስክ ሉዓላዊነት ሀገራት በውስጣዊም ሆነ በውጭ ጉዳዮቻቸው ላይ ያለማንም ጣልቃ ገብነት በነፃነት የመወሰን ሙሉ ባለቤትነትን ማረጋገጥ መቻል ነው። ከለውጡ በኋላ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟን ማዕከል ያደረገ የዲፕሎማሲ አካሄድ እየተከተለች እንደምትገኝ ገልፀው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ መጠናቀቅና ወደ ሥራ ማስገባት የመወሰን ነጻነት የታየበት ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ሕጋዊና ሞራላዊ መሠረት ያለው የባህር በር የማግኘት ጥያቄን በማንሳት ለዓለም ማህበረሰብ የማስገንዘብ ተግባር እያከናወነች መሆኗም የውሳኔ ሉዓላዊነቷ ማሳያ መሆኑን አንስተዋል። በሀገር ውስጥ እየተከናወኑ ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች የኢትዮጵያን ሁለተናዊ ዕድገት ከማረጋገጥ ባለፈ፣ ለአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነቶች መጠናከር ያላቸውን ቁልፍ ሚና በግልጽ ያሳያሉ ብለዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል ዶክተር መብራቱ አለሙ በበኩላቸው የዲፕሎማሲ አቅም ከሀገር ውስጥ የኢኮኖሚ ጥንካሬ ጋር የተሳሰረ መሆኑን ገልፀዋል። ባለፉት የለውጥ ዓመታት መንግስት ወደ ተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ትግበራ መግባቱ የውጭ ምንዛሬ እጥረት፣ የዕዳ ጫናና የዋጋ ንረት ችግሮችን መፍታት ማስቻሉን አንስተዋል። የግል ዘርፉን በማጠናከር፣ የውጭ ባንኮችና ካፒታል ወደ ሀገር እንዲገቡ በር በመክፈትና የካፒታል ገበያን ስርዓትን በመዘርጋት የሀገሪቱን የፋይናንስ አቅም ማሳደጉን ገልፀዋል። በኢትዮጵያ እየተተገበረ ያለው የብዝሃ ዘርፍ ኢኮኖሚም የኤክስፖርት መጠንን በማሳደግና በብድርና በእርዳታ ላይ ያለውን ጥገኝነት በመቀነስ የውሳኔ ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የሚያስችል መሆኑን ተናግረዋል። በከተሞች በኮሪደር ልማት እየተመዘገበ ያለው ፈጣን እድገት የሀገሪቱን ዓለምአቀፍ ገጽታና የኮንፍረንስ ቱሪዝም ማዕከልነት እያሳደገ መሆኑንም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟን ማዕከል ያደረገ ባለብዙ ዘርፍ ዲፕሎማሲና ለጎረቤት ሀገራት ቅድሚያ የመስጠት መርህን እየተከተለች መሆኗም ለዲፕሎማሲ ስኬቷ መሰረት መሆኑን ምሁራኑ ተናግረዋል።
በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በልማትና በመልካም አስተዳደር ዘርፎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል
Jul 20, 2026 711
ገንዳ ውሃ፤ ሐምሌ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በምዕራብ ጎንደር ዞን በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በልማትና በመልካም አስተዳደር ዘርፎች ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ያደረጉ ውጤታማ ተግባራትን ለማስመዝገብ መቻሉን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። ​የዞኑ አስተዳደር የተጠናቀቀው በጀት ዓመት የመንግስትና የፓርቲ ስራ አፈፃፀም ግምገማና የቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ያተኮረ የውይይት መድረክ አካሄዷል።   ​የምዕራብ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ እያሱ ይላቅ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የተጠናቀቀው በጀት ዓመት ህዝቡ የሚያነሳቸውን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት ጥረት የተደረገበት ነው። በተለይም ህብረተሰቡን በማሳተፍ የተከናወኑ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች፣ የትምህርትና የጤና ተደራሽነትን የማስፋፋት ተግባራት ተጨባጭ ውጤት የታየባቸው መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ ውስጥም የተጠናቀቁ የመንገድ፣ የንፁህ መጠጥ ውሃ ፣ የጤና ተቋማት ግንባታና ሌሎች የመሰረተ ልማት ስራዎችን ለአብነት የሚጠቀሱ ናቸው ብለዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም የተመዘገቡ ስኬቶችን አጠናክሮ በማስቀጠል የህዝቡን ጥያቄዎች ሙሉ በሙሉ ለመመለስ መላው አመራርና ህዝቡ በቁርጠኝነት ሊረባረቡ እንደሚገባ አሳስበዋል። ​በብልጽግና ፓርቲ የማእከላዊ ጎንደር ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ እንዳለው ማሩ በበኩላቸው፤ በበጀት ዓመቱ የተመዘገቡት ውጤቶች በአመራሩና በአባላቱ የተቀናጀ ጥረት የተገኙ ናቸው ብለዋል።   የተመዘገቡት ውጤቶች የመንግስት መዋቅሩ ፓርቲው በሚያስቀምጠው አቅጣጫ መሰረት መፈጸም በመቻሉ የመጣ ስኬት መሆኑን ጠቁመው ይህም በአዲሱ በጀት ዓመት ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል። ​በተጠናቀቀው በጀት ዓመት የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥ አመርቂ ውጤት ተመዝግቧል ያሉት ደግሞ የዞኑ ግብርና መምሪያ ምክትል ኃላፊ ጤናው ፋንታሁን ናቸው።   በዚህም በመኸርና በመስኖ ልማት ከ11 ነጥብ አምስት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት መቻሉን አውስተዋል። በአዲሱ በጀት ዓመትም የተጀመሩ የግብርና ምርትና ምርታማነት ማሳደጊያ ስራዎችና የቴክኖሎጂ አጠቃቀምን ይበልጥ አጠናክሮ ለማስቀጠል በተለየ ትኩረት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል። በመድረኩ የዞኑ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።
ተመካካሪዎች በተመደቡባቸው አጀንዳዎች ላይ መምከር ጀምረዋል-ኮሚሽነር መሐሙድ ድሪር
Jul 20, 2026 845
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 13/2018(ኢዜአ)፦ የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ተመካካሪዎች በተመደቡባቸው አጀንዳዎች ላይ ዛሬ መምከር መጀመራቸውን የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር መሐሙድ ድሪር ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር አምባሳደር መሐሙድ ድሪር ፣ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ አስመልክቶ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥተዋል። የምክክር ጉባኤው ተመካካሪዎች በተለያዩ ቡድኖች ተከፋፍለው በተመደቡበት አጀንዳ ላይ መመካከር መጀመራቸውን ኮሚሽነሩ ተናግረዋል። ዛሬ የተጀመረው ሂደት የምክክሩ ቁልፍ አካል መሆኑን ጠቅሰው፥ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተወጣጡ በርካታ ሀሳቦች እንደሚንሸራሸሩበት ጠቁመዋል። ኮሚሽኑ ልምድ ያላቸው አመካካሪዎችን በመመደብ የምክክሩን ሂደት እየተከታተለ መሆኑን ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም መጀመሩ ይታወቃል።
በሀገራዊ ምክክሩ ለዜጎቿ ሁሉ የምትመች ሀገር ለመገንባት የሚያስችል ታሪካዊ አጋጣሚ ላይ እንገኛለን
Jul 20, 2026 747
ጅማ፤ ሀምሌ 13/2018(ኢዜአ)፡- በሀገራዊ ምክክሩ ለዜጎቿ ሁሉ የምትመች ሀገር ለመገንባት የሚያስችል ታሪካዊ አጋጣሚ ላይ እንገኛለን ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ከህዝብ የሰበሰባቸውን አጀንዳዎች ለይቶ እና አደራጅቶ ለምክክሩ ይፋ ባደረጋቸው አጀንዳዎች ላይ በአዲስ አበባ የምክክር ጉባኤ በማካሄድ ላይ መሆኑ ይታወቃል። የምክክር ሂደቱ የኢትዮጵያን የቆዩ ስብራቶች በማከም የጸናችና ለትውልዱ የምትመች ሀገር ለመገንባት ጠንካራ መሰረት ለማኖር የሚያስችል እንደሚሆን ይታመናል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፤ በምክክር ጉባኤው መክፈቻ ላይ ባደረጉት ንግግር በምክክሩ ከየሰፈራችን ወጥተን ለኢትዮጵያ ስንመክር፣ ለልጆቻችን ስንልና እነርሱን እያሰብን ስንወያይ ውጤቱ ፍሬያማ ይሆናል ማለታቸው ይታወቃል። በመሆኑም የምክክሩን ውጤት ስኬታማ በማድረግ የኢትዮጵያን ሀገረ መንግስት ማጽናትና ለዜጎቿ ሁሉ የምትመች ሀገር ለመገንባት የሚያስችል ታሪካዊ አጋጣሚ ላይ እንገኛለን ሲሉ ኢዜአ ያነጋገራቸው የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገልጸዋል። በጅማ ዩኒቨርሲቲ የሚዲያ እና ኮሚኒኬሽን ትምህርት ክፍል መምህር ጌታቸው ጥላሁን (ዶ/ር)፤ የመነጋገር ባህል ሲዳብር በውይይት የሚያምን ዘመናዊና ጠንካራ ትውልድ የሚፈጠር ይሆናል ብለዋል። በኢትዮጵያ ከምክክር ይልቅ በሃይልና በጉልበት ለግጭትና ጦርነት የተዳረግንበት አጋጣሚ የበዛ ነው ያሉት ዶ/ር ጌታቸው፤ ሀገራዊ ችግሮችን ለመቋጨት ከምክክር የተሻለ አማራጭ አይኖረንም ብለዋል። በመሆኑም የኢትዮጵያን ሀገረ መንግስት ማጽናትና ለዜጎቿ ሁሉ የምትመች ሀገር ለመገንባት የሚያስችል ታሪካዊ አጋጣሚ ላይ በመሆናችን በአግባቡ ልንጠቀምበት ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። በምክክር ኮሚሽኑ የተለዩ አጀንዳዎችን ሀገራዊ ችግሮችን በዘላቂነት መፍታት የሚያስችሉ ቁልፍ ነጥቦች መሆናቸውን ገልጸዋል። በቡሌ ሆራ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስ እና ውጭ ግንኙነት መምህር ነጋሳ ገላና፤ ከግጭትና የጦርነት አዙሪት በመውጣት ለዜጎቿ የምትመች ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት በምክክር ኢትዮጵያን ማጽናት ይገባል ብለዋል። በኢትዮጵያ ምክክሩ ነፃ አካታችና ሁሉንም አሳታፊ በሆነ መልኩ እየተካሄደ በመሆኑ ትልቅ ስኬት የሚመዘገብበት እንደሚሆን ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የተለዩ የምክክር አጀንዳዎች የኢትዮጵያን ችግሮች በአግባቡ የለዩና በምክክር መፍትሄ ሊያመጡ የሚችሉ ስለመሆናቸው አንስተዋል። ሀገራዊ ምክክር የውስጥ ችግሮችን በራስ አቅም ለመፍታት መንገድ ስለሚከፍት፣ መበታተናችንን የሚሹ አካላት በሀገሪቱ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ የሚገቡበትን ቀዳዳ የሚዘጋ ስለመሆኑም አስረድተዋል።  
የምክክር ሂደቱ ለኢትዮጵያ እና ህዝቦቿ መፃኢ እድል ትልቅ ተስፋ የተሰነቀበት ነው
Jul 20, 2026 741
ጎንደር፤ ሃምሌ 13/2018(ኢዜአ)፡- የምክክር ሂደቱ ለኢትዮጵያ እና ህዝቦቿ መፃኢ እድል ትልቅ ተስፋ የተሰነቀበት በመሆኑ በአግባቡ ልንጠቀምበት ይገባል ሲሉ የተለያዩ የሃይማኖት አባቶች ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ከህዝብ የሰበሰባቸውን አጀንዳዎች ለይቶ እና አደራጅቶ ለምክክሩ ይፋ ባደረጋቸው አጀንዳዎች ላይ በአዲስ አበባ የምክክር ጉባኤ በመካሄድ ላይ መሆኑ ይታወቃል። የኢትዮጵያን የቆዩ ስብራቶች በማከም የጸናችና ለትውልዱ የምትመች ጠንካራ ሀገር ለመገንባት ምክክሩ አዲስ የታሪክ ምእራፍ የሚከፍት መሆኑ ይታመናል። በዚሁ ጉዳይ ላይ በጎንደር ከተማ ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ የኃይማኖት አባቶች የምክክር ሂደቱ ለኢትዮጵያ እና ህዝቦቿ መፃኢ እድል ትልቅ ተስፋ የተሰነቀበት በመሆኑ በአግባቡ ልንጠቀምበት ይገባል ብለዋል። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኃይማኖት አባት መላከ ገነት ቀሲስ ፈንታ ገብረሚካኤል፤ ለኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ከምክክር የሚሻል አማራጭ የለም ሲሉ ተናግረዋል። በምክክር ችግሮች ሲፈቱ ነጋዴው ነግዶ የሚያተርፍበት፣ ገብሬው አርሶ የሚያመርትበት፣ የትኛውም ዜጋ ተንቀሳቅሶ ሃብት በማፍራት ለሀገር እድገት የድርሻውን የሚወጣ ይሆናል ብለዋል። በመሆኑም ከጥላቻና የከረረ ተቃርኖ በመውጣት በምክክር ችግሮችን መፍታት እንደሚቻል ጠንካራ አቋም በመያዝ ለስኬታማነቱ መስራት ይገባናል ሲሉ ገልጸዋል። የጎንደር ከተማ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት ዋና ፀሐፊ ሐሰን ደሴ (ዶ/ር)፤ በኢትዮጵያ ከግጭትና ጦርነት አዙሪት ልንወጣ ያልቻልነው ለምክክር ቦታ በመስጠት ችግሮችን መፍታት ባለመቻላችን ነው ብለዋል። በመሆኑም ሀገራዊ የምክክር ሂደት መካሄዱ ለኢትዮጵያና ህዝቦቿ ትልቅ እድል መሆኑን አንስተው በአግባቡ ልንጠቀምበት ይገባል ሲሉ ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ብዝሃ ማንነቶችና ሃይማኖቶች ያሉ በመሆኑ በልዩነቶች ውስጥ መመካከርና መደማመጥ የግድ መሆኑንም አንስተዋል። የካዶሽ ወንጌላዊያን አማኞች ጎንደር አጥቢያ መጋቢ የሆኑት መጋቤ እልፍነህ ተስፉ፤ የሀገርን አንድነት ማስቀጠል የሚቻለው በምክክር ለችግሮች ዘላቂ መፍትሄ በመስጠት ብቻ ነው ብለዋል። ሌሎች ብዝሐ ማንነት ያላቸው ሀገሮች ችግር በገጠማቸው ጊዜ ተግዳሮታቸውን የፈቱት በምክክር እንጂ በጦርነት አለመሆኑን አንስተው እኛም ይህንኑ የምክክር እድል በአግባቡ መጠቀም አለብን ሲሉ ተናግረዋል።  
ሀገራዊ ምክክሩ ጠንካራ ሀገር ለመገንባት መሰረት ይጥላል
Jul 20, 2026 754
አርባ ምንጭ/ወላይታ ሶዶ፤ሐምሌ13/2018 (ኢዜአ)፦ሀገራዊ ምክክሩ አለመግባባቶችን በውይይት በመፍታት ጠንካራ ሀገር ለመገንባት መሰረት እንደሚጥል የአርባ ምንጭ እና የወላይታ ሶዶ ከተሞች ነዋሪዎች ገለጹ። በሀገሪቱ ዘመናትን ያስቆጠሩ አለመግባባቶች በውይይት ለመፍታት ቁልፍ መሳሪያ የሆነው ሀገራዊ ምክክር በርካታ ሂደቶችን አልፎ ወደመቋጫ ምዕራፍ ደርሷል። ኢዜአ ይህን ታሪካዊ መድረክ በማስመልከት የአርባ ምንጭ እና የወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪዎችን አነጋግሯል። አስተያየታቸውን የሰጡ ነዋሪዎች እንደገለጹት፥ ይህንን ሀገራዊና ታሪካዊ ምክክር በሰለጠነ መንገድ በመጠቀም ለውጤት ማብቃት የቆዩና ላለመግባባት መንስኤ የሆኑ ችግሮችን ለመፍታት ወሳኝ ሚና ይጫወታል። ከአስተያየት ሰጪዎች መካከል የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪ አቶ ድኮርሳ ከበደ እንዳሉት፥ ምክክሩ የሀገሪቱን ዘላቂ ሰላምና ዕድገት ለማስቀጠል ታሪካዊ አጋጣሚ ነው።   ለምክክር ተለይተው የቀረቡ አጀንዳዎችም የኢትዮጵያን የዘመናት ችግሮች ለመፍታት የሚያስችሉና ህዝቡ በየደረጃው በተዘጋጁ መድረኮች ያነሳቸውን መሰረታዊ ጥያቄዎችን ያንጸባረቁ ናቸው ብለዋል። ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ ኢንጂነር ጽዮን አረጋ በበኩላቸው፤ ምክክሩ ለነገው ትውልድ የተሻለችና የተረጋጋች ሀገር ለማውረስ ትልቅ ዕድል መሆኑን አንስተዋል።   በሃሳብ ልዕልና ላይ በመመስረት ልዩነቶችን ማስታረቅ የሚችል ስልጡን ማህበረሰብ ለመገንባት ምክክሩ ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ጠቁመዋል። ሀገራዊ ምክክሩ ጠንካራ ሀገረ-መንግስት ለመገንባት የምናደርገው የጋራ ጉዞ ነው ያሉት ደግሞ አቶ አየለ አፋ ናቸው። የምክክር አጀንዳዎቹ ለዘመናት የቆዩ ሀገራዊ ችግሮችን በዘላቂነት በመፍታትና በህዝቦች መካከል አንድነትን ለማጠናከር ወሳኝ መሆናቸውን ተናግረዋል።   የተጀመረው ምክክር ችግሮችን በሰለጠነ መንገድ በጋራ ተወያየቶ ለመፍታት እና አንድነቷ የተጠናከረና የበለጸገች ሀገር ለማጽናት መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን አስረድተዋል። ከወላይታ ሶዶ ከተማ ነዋሪዋች መካከል ወይዘሮ የአብስራ ደለለኝ ለሀገራዊ ምክክሩ የተመረጡት አንኳር አጀንዳዎች በሀገሪቱ የቆዩ ቅሬታዎችን ለመፍታት የሚያግዙ መሆናቸውን ገልጸዋል። ምክክሩ በሀገር ጉዳይ ላይ የጋራ መግባባት ለመፍጠር ወሳኝና ታሪካዊ ዕድል መሆኑን የጠቀሱት ደግሞ የዚሁ ከተማ ነዋሪ አቶ አሸናፊ ዳንሳ ናቸው። ለቀጣዩ ትውልድ ሰላሟ የጸና፣አንድነቷ የተረጋገጠና የበለጸገች ሀገር ለማስረከብ ሀገራዊ ምክክሩን ውጤታማ ማድረግና በስኬት ማጠናቀቅ የሁሉም ሃላፊነት ሊሆን ይገባል ብለዋል።
በምክክር መግባባት ለኢትዮጵያ መፅናት
Jul 20, 2026 197
በኢትዮጵያ ለዘመናት ስር የሰደዱ የፖለቲካ ልዩነቶች ዛሬም ድረስ ሀገራዊ ችግሮች ሆነው በመቀጠላቸው በህዝቡ ማህበራዊ ትስስር፣በዘላቂ ሰላም፣በኢኮኖሚ ልማትና በሀገሪቱ ሁለንተናዊ ብልጽግና ላይ ያሳደሩት አሉታዊ ተጽዕኖና ያስከተሉት ጠባሳ የጎላ ነው። ይህም ልዩነቶች በውይይትና በሰላማዊ መንገድ ካለመፈታታቸው የተነሳ ነው። ለዚህ ነው በኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ተቋቁሞ የቆዩ የፖለቲካ ችግሮችን እና አለመግባባቶችን በውይይት ለመፍታት ተግባራዊ እንቅስቃሴ የተጀመረው። ኢትዮጵያዊያንም ሀገራዊ ምክክርን ወደ የጋራ መግባቢያ መድረሻ መንገዳቸው በማድረግ እየተጠቀሙበት ይገኛል። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽንም ከ4 ሺህ በላይ ኢትዮጵያዊያን ለዘመናት ሳያግባቡ የቆሙ ችግሮቻቸውን ተገናኝተው በመነጋገር እንዲፈቱ እድል አመቻችቷል። ሀገራዊ ምክክሩ ከሐምሌ 8 ጀምሮ በአዲስ አበባ በስኬት እየተካሄደ ሲሆን ይዚህ ታሪካዊ ምክክርም ተሳታፊ ባለድርሻ አካላት ያለምንም ልዩነት ሃሳባቸውን በነጻነት የሚያነሱበት እውነተኛ የአካታችነት ማሳያ ሆኗል። በኢትዮጵያ የሐሳብ ገበያን ባሕል ለማድረግ ተግባራዊ ከሚደረጉ መንገዶች አንዱ ሀገራዊ ምክክር የሆነውም ለዚህ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በመደመር መንግሥት መጽሐፍ ገጽ 384 ላይ እንዲህ ይላሉ፦ በሀገረ-መንግሥት ዋና ዋና ጉዳዮች ላይ ሕዝብ ተመካክሮ፣ የጋራ መግባባት ላይ ደርሶ፣ የተግባባባቸውን በሕግና በሥርዓት አጽንቶ፤ ያልተግባባባቸውን ለወደፊት ምክክሮች አቆይቶ አልተጓዘም።በዚህ የተነሣ በየጊዜው ቅሬታ፣ ኩርፊያ፣ አብዮት፣ ዐመጽ ይፈጠራል። ነገሮች በተናጠል እየቀረቡ ለፖለቲካ ነጋዴዎች ምቹ ሁኔታ ይመቻቻል። ሁለንተናዊ ዕይታ ይጠፋል።ሀገራዊ ምክክር ይህን የዘመናት ስብራት ይጠግናል። በመደመር መንግሥት መጽሐፍ (ገጽ 383) ላይ እንደሰፈረው ደግሞ፤ በኢትዮጵያ የሚደረገው ሀገራዊ ምክክር የተለያዩ ሐሳቦች በአንድ መድረክ ቀርበው፤ በምክክርና ውይይት ጎልብተው አሰባሳቢና አስማሚ ሆነው የሚወጡበት መድረክ ነው። ስለሀገር የሚያገባው ሁሉም አካል በመሠረታዊ ጉዳዮች ላይ ሐሳብ አዋጥቶና ተነጋግሮ መግባባት የሚፈጥርበት ምኅዳር መሆኑም ተገልጿል። ይህ በሀገር በቀል ልምድና እውቀት ላይ የተመሰረተ ምክክር ለነገዋ ኢትዮጵያ የሚያበረክተው አስተዋጽኦ እጅግ የጎላ ስለሆነ ነው።በሂደቱ የሚደረጉ ውይይቶችና የሚደረሱ ስምምነቶች የሀገሪቱን ፖለቲካዊ መግባባቶች የሚያጠናክሩ ናቸው። የጋራ ብሄራዊ ትርክት ለመገንባት፣ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ፣ የህግ የበላይነትን ለማስፈንና የኢኮኖሚ ብልጽግናን ለማፋጠን መሰረት ይሆናሉ። በመሆኑም ልዩነቶችን በውይይት ፈትቶ፣ለትውልድ ተስፋ የምትሆን፤በሰላምና በአንድነት የደመቀች ሀገር ለመገንባት ሀገራዊ ምክክሩ እጅግ አስፈላጊ ነው። በዚህም ለጋራ ሀገር፤የጋራ ምክክር በማድረግ ልዩነቶች በውይይት በመፍታት ኢትዮጵያን ለማፅናት ይህ ታሪካዊ አጋጣሚ እንዲሳካ ሁሉም የበኩሉን ድጋፍ ሊያደርግ ይገባል።
የትግራይ ሕዝብ ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት በትክክል ያንጸባረቀ ስኬታማ ሰልፍ ተካሂዷል 
Jul 19, 2026 446
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦ የትግራይ ሕዝብ ድምጹን ያሰማበትና ለሰላም ያለውን ቁርጠኝነት በትክክል ያንጸባረቀ ውጤታማ ሰልፍ መካሄዱን የትግራይ የሰላምና ለውጥ ምክር ቤት ገለጸ። በትግራይ ሕዝብ ላይ እየተፈጸመ ያለውን አፈና እና ጭቆና የሚያወግዝ እንዲሁም የጦርነት ዝግጅትን የሚቃወም ታላቅ ሰላማዊ ሰልፍ ትናንት በአዲስ አበባ ከተማ መስቀል አደባባይ ተካሄዷል። በትግራይ የሰላምና ለውጥ ምክር ቤት "አፈሳ ይቁም፣ ሰላም ይስፈን” በሚል መሪ ሐሳብ በተዘጋጀው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ በአዲስ አበባና በአካባቢው የሚኖሩ የትግራይ ክልል ተወላጆች፣ የሲቪክ ማህበራትና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል። ሰልፉን በተመለከተ የትግራይ የሰላምና ለውጥ ምክር ቤት መግለጫ ሰጥቷል። የምክር ቤቱ የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ነጋ አሰፋ ሰልፉን በተመለከተ ዛሬ በሰጡት መግለጫ እንደገለጹት፤ የትግራይ ተወላጆችና ሌሎች የከተማዋ ነዋሪዎች በነቂስ በመውጣት ድምፃቸውን አሰምተዋል። ሰላማዊ ሰልፉ የተለያዩ ዓላማዎችን አንግቦ የተካሄደ ሲሆን፤ ስኬታማ ሆኖ መጠናቀቁን አስታውቀዋል። ሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት በመጣስ እየፈጸመ ያለው ድርጊት የትግራይን ሕዝብ በእጅጉ እንዳሳሰበው ገልጸው፤ ሰልፉ ስምምነቱ በአስቸኳይ እንዲተገበር የተጠየቀበት መሆኑን ተናግረዋል። ወጣቶች ወደ ጦርነት እንዲገቡ እየተደረገ ያለው አስገዳጅ አፈሳ ወንጀል መሆኑን የገለጹት የምክር ቤቱ የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ነጋ፤ ይህንም ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ የማሳወቅና ድርጊቱ በአስቸኳይ እንዲቆም መልዕክት የተላለፈበት ሰልፍ እንደነበር አብራርተዋል። ሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን እያደረገ ያለውን የጦርነት ዝግጅት እንዲያቆም የትግራይ ሕዝብ ግልጽ መልዕክት ያስተላለፈበት ሰልፍ መሆኑንም ተናግረዋል። ሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን የሕዝቡን ተቃውሞ ለመመከት መድረኮችን እየጠራ በኃይል ለማስፈራራትና ለማስገደድ መሞከሩን ጠቁመው፤ ሕዝቡ ግን ለሰልፉ ያለውን ድጋፍ ቤቱ በመቀመጥ በተግባር አሳይቷል ብለዋል። ሕዝቡ ትግራይን ድጋሚ ወደ ጦርነት ለመክተት እየተደረገ ያለውን ጥረት አጥብቆ እየተቃወመ እንደሚገኝም አመልክተዋል። የትግራይን ሰቆቃ ለማስቀረት የምንሰራውን ሥራ እናጠናክራለን ያሉት ኃላፊው፤ለዚህም ሁሉም በጋራ እንዲቆም ጥሪ አቅርበዋል። ሰልፉ እንዲሳካ አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላት በሙሉ ምስጋና አቅርበው፣ መሰል የሕዝብ ድምፅ ማሰሚያ ሰልፎች በሌሎችም አካባቢዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቁመዋል።
ከኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ለመላው ኢትዮጵያዊያን የተላለፈ መልዕክት
Jul 19, 2026 418
በሀገራችን ኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ እየተከናወነ ያለውና ሁሉም ኢትዮጵያዊያን ሀገራዊ ፋይዳ ባላቸው እጅግ መሰረታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በጋራ የሚመካከሩበት ታሪካዊ የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ እንዲሳካ ዜጎች ራሳቸውን ከሀሰተኛ መረጃ በመጠበቅ እና በኮሚሽኑ ላይ ሙሉ እምነት በማሳደር ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጥሪ ያቀርባል፡፡ ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም የተጀመረውን ታሪካዊው የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ በተመለከተ አንዳንድ ግለሰቦችና ቡድኖች በማህበራዊ ሚዲያ አውታሮች አማካኝነት ከእውነታ የራቁ መረጃዎችን እያሰራጩ መሆኑን ኮሚሽኑ ደርሶበታል፡፡ ኮሚሽኑ የመናገር ነጻነትን ሙሉ በሙሉ የሚያከብር ገለልተኛ ተቋም እንደመሆኑ ገንቢ የሆኑ ሃሳቦችንና ውይይቶችን የሚቀበል ቢሆንም ሰፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ በሀሰተኛ መረጃዎች እንዳይታለል አስፈላጊውን ክትትል በማድረግ ለህዝብ ይፋ ለማድረግ ይገደዳል፡፡ ሀገራዊ ምክክሩ የሁሉም ኢትዮጵያዊያን ነው። የዚህ ሂደት ስኬት የሚወሰነው ዜጎች በትዕግስት፣ በጥበብ እና በጋራ የኃላፊነት ስሜት ለመሳተፍ በሚያሳዩት የጋራ ቁርጠኝነት ላይ ነው። ይህም እየተከናወነ ይገኛል፡፡ ሂደቱ ተጀመረ እንጂ ውጤቱ ገና ነው፡፡ ይህንን ውጤት በትዕግስት መጠበቅ ደግሞ ከመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሚጠበቅ ይሆናል፡፡ ሐምሌ 8 ቀን 2018 ዓ.ም የተጀመረው የሀገራዊ ምክክር ጉባኤ ኮሚሽኑ ባወጣቸው የአሰራር ሂደቶች መሰረት እየተከናወነ ይገኛል፡፡ በዚህ መሰረት ባለፉት አራት ቀናት ኮሚሽኑ የጉባኤው ተሳታፊዎች የተጣለባቸውን ትልቅ ሀገራዊ ኃላፊነት በአግባቡ እንዲወጡ እርስ በእርስ እንዲተዋወቁ ማድረግን ጨምሮ ለሂደቱ ጠቃሚ በሆኑ የእውቀት እና የስነ-ልቦና ዝግጅቶች እንዲያደርጉ መደላድሉን ፈጥሯል፤ ይህም የሀገራዊ ምክክር ጉባኤው አንድ አካል መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡ ይህ እየሆነ ባለበት አንዳንድ ግለሰቦችና ቡድኖች በማህበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ኮሚሽኑ ምክክሩን ለመጀመር እክል እንደገጠመው የተሳሳተ መረጃ ሲያሰራጩ ተመልክተናል፡፡ በመሆኑም መሰል የተሳሳቱ መረጃዎች የራሳቸው ዓላማ ባላቸው ግለሰቦችና ቡድኖች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ስለሚችሉ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በየእለቱ የሚኖሩ የምክክር ሂደቶችን ኮሚሽኑ ከሚሰጣቸው መግለጫዎችና የምክክሩን ሂደት ለመዘገብ በስፍራው ከተገኙ መገናኛ ብዙኃን ብቻ በመከታተል ራሱን ከተሳሳቱ መረጃዎች በመጠበቅ የምክክሩን ሂደት እንዲደግፍ ኮሚሽኑ ጥሪ ያቀርባል፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም
ጽኑ ሰላምና ልማት እንጂ የሕገ-ወጡን የሕወሓት ቡድን የጦርነት ዳንኪራ አንፈልግም
Jul 19, 2026 349
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦የትግራይ ክልል ወጣትና ህዝብ ጽኑ ሰላምና ልማት እንጂ የሕገ-ወጡን የሕወሓት ቡድን የጦርነት ዳንኪራ እንደማይፈልግ የሕገ-ወጡን ቡድን አፈሳና አፈና ሸሽተው አዲስ አበባ የመጡ ወጣቶች ገለጹ። በትግራይ የሰላምና ለውጥ ምክር ቤት አስተባባሪነት ሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን በትግራይ ክልል ሕዝብ ላይ እየፈጸመ ያለውን አፈሳና አፈና በመቃወም በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሂዷል። ''አፈሳ ይቁም፤ ሰላም ይስፈን'' በሚል መሪ ሃሳብ በተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ የክልሉ ተወላጆች፣ ግፍን በመሸሽ ወደ አዲስ አበባ የመጡ ወጣቶች፣ የሲቪክ ማህበራትና የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል። አፈሳና አፈናውን በመሸሽ ወደ አዲስ አበባ የመጡ ወጣቶች ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን የክልሉን ወጣቶች በግዳጅ በማፈስ ወደ ጦር ካምፖች እያጋዛቸው ይገኛል። ሕገ-ወጥ ቡድኑም የክልሉን ወጣቶች ለሱዳንና ሻቢያ የጥፋት ኃይሎች በመሸጥ ሰብዓዊ ክብርን የሚጋፋ ኢ-ሰብዓዊ ግፍ እየፈጸመ እንደሚገኝ አስረድተዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል ወጣት ሶሎሞን እምባዬ፤ ጦርነት ናፋቂው ሕገ-ወጥ ቡድን ካለፈው ስህተቱ ሳይማር ለዳግም ጦርነት እየተዘጋጀ እንደሚገኝ ገልጿል። የጦርነት ነጋዴው ሕገ-ወጥ ቡድን ፅምዶ በተሰኘ የጥፋት ጥምረት ወጣቶችን በየቤተ-ዕምነቱ፣ በገበያና በየመንገዱ ለቅሞ በመውሰድና ለውጭ ገበያ ጭምር በመሸጥ እናቶችን እያስለቀሰ መሆኑን ተናግሯል። የትግራይ ሕዝብ ፍላጎት ጽኑ ሰላምና ልማት ብቻ መሆኑን ያነሳው ወጣቱ፤ እናቶችም የጦር መሳሪያ ካነገበው ኃይል ጋር በመጋፈጥ ተቃውሟቸውን እያሰሙ መሆናቸውን አክሏል። ፌዴራል መንግሥትም የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት በማፍረስ ሕገ-ወጡ የሕወሓት ቡድን ከፀረ-ሰላም ኃይሎች ጋር በፈጠረው የጥፋት ጥምረት በሕዝቡ ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍና መከራ እንዲያስቆም ጥሪ አቅርቧል። ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ወጣት እምሩ ብርሃኑ በበኩሉ፤ ሕገ-ወጡ ቡድን ወጣቶችን ለውጭ ኃይሎች በመሸጥ የገቢ ምንጭ ማድረጉ የአደባባይ ምስጢር ከሆነ መሰነባበቱን ገልጿል። በሀገር ውስጥና በውጭ የሚኖሩ የትግራይ ክልል ወጣቶችና ሕዝብም የቡድኑን የጦርነት ጉሰማ በመታገል ሰላም ፈላጊነታቸውን በተግባር ሊያሳዩ እንደሚገባ አሳስቧል። ወጣት መብራህቱ ኻልአዩ በበኩሉ፤ ቡድኑ በክልሉ የከፈተው የአፈሳና የአፈና ጭቆና ሕዝብን ለስቃይ፣ ወጣቶችን ደግሞ ለስደት መዳረጉን ጠቁሟል። አክሎም ቡድኑ ወጣቶችን በማፈን ከሚፈፅመው ግፍ በተጨማሪም አርሶ አደሩ የእርሻ ሥራውን በአግባቡ እንዳያከናውን ተጽዕኖ እየፈጠረ መሆኑን ተናግሯል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም