ፖለቲካ
መንግስት ለሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ተግባራዊነት በቁርጠኝነት ይሰራል-- ተስፋዬ በልጅጌ
Apr 19, 2024 429
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ መንግስት ለሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ተግባራዊነትና ውጤታማነት በቁርጠኝነት እንደሚሰራ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ ገለጹ። የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈጉባኤን ጨምሮ የዴሞክራሲ ተቋማት አመራሮችና ሌሎች በተገኙበት በሽግግር ፍትህ ፖሊሲና የፌደራል የአስተዳደር ስነ-ስርአት አዋጅ ላይ ውይይት ተካሂዷል፡፡ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ በዚሁ ጊዜ የተለያዩ የዓለም አገራት ከተወሳሰበ ችግርና ቀውስ ለመውጣት የሽግግር ፍትህን መፍትሄ አድርገው መጠቀማቸውን አንስተዋል፡፡ በኢትዮጵያም በቀደሙ ስርዓቶች የተፈጸሙ ሰብዓዊ መብት ጥሰቶች፣ በታሪክ ምክንያት የሚነሱ አለመግባባቶች፣ የዴሞክራሲ ስርዓት አለመጎልበት፣ ለዘመናት የተከማቹ የፖለቲካ ቀውሶች መኖራቸውን ጠቅሰው፤ ለእነዚህ ችግሮች እልባት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል፡፡ ከዚህ አኳያ ከአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ጋር የሚመጋገብና ሂደቱን የሚያሳልጥ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። መንግስት ፖሊሲው እንዲዘጋጅ ከማድረግ ጀምሮ ቁርጠኛ የፖለቲካ አቋም መውሰዱን ገልጸው፤ይህም ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን አብራርተዋል፡፡ የአሁኑ ትውልድ ችግሮችን ቀርፎ ኢትዮጵያን ወደ አዲስ ምእራፍ የማሸጋገር ኃላፊነት እንዳለበትም ነው የተናገሩት፡፡ ፖሊሲ ለረዥም ጊዜ ስር የሰደዱ ችግሮችን በመፍታት ከችግር መውጫ አንዱ መሳሪያ መሆኑንም አጽኖት ሰጥተው ተናግረዋል። የትናንት ቁርሾዎችን በእርቀ ሰላምና ይቅርታ በመዝጋት ለነገ ትውልድ የተረጋጋችና ዘላቂ ሰላም የሰፈነባት አገር ማስተላለፍ እንደሚገባም አንስተዋል፡፡ በዚህ ረገድ መንግስት የሚጠበቅበትን ሁሉ ለማገዝ ዝግጁ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የመድረኩ ተሳታፊዎች በበኩላቸው ለፖሊሲው ተፈጻሚነት በጋራ መስራት እንደሚገባ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ የፖሊሲው ወቅታዊነትን በሚመለከትም ከተሳታፊዎች ጥያቄ ቀርቧል፡፡ አቶ ተስፋዬ በልጅጌ በምላሻቸው አገራዊ የሆኑ ችግሮች በይደር የሚታለፉ አለመሆናቸውን ጠቅሰው፤ ችግሮቹን በአንድነት ለመፍታት ጊዜው አሁን መሆኑን አስረድተዋል። በኢትዮጵያ ገለልተኛ ተቋማትን በማደራጀት ነጻና ገለልተኛ ሆነው እንዲሰሩ ለማድረግ የተጀመረው ስራ ለፖሊሲው ተፈጻሚነትም አስቻይ ሁኔታዎችን እንደሚፈጥርም አንስተዋል። በሌላ በኩል የፌደራል የአስተዳደር ስነ-ስርአት አዋጅ የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠትና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን ሚናው የጎላ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡ አዋጁ አጠቃላይ የተጀመረው ለውጥ ስራ አካል መሆኑን በመጥቀስ ይህም የአሰራር ማነቆዎችን በመፍታት፣ አደረጃጀትን በማስተካከል፣ አገልግሎትን በማሻሻል ከፍተኛ ጠቀሜታ አለው ነው ያሉት። አዋጁ የታለመለትን ዓላማ እንዲያሳካ የተቋማት ኃላፊዎችና ሙያተኞች ተግባራዊነቱ ላይ በልዩ ትኩረት መስራት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል።    
አቶ አደም ፋራህ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ጋር ተወያዩ
Apr 19, 2024 325
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ የብልፅግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አደም ፋራህ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ዣዎ ዢዋን ጋር ተወያይተዋል፡፡ በውይይታቸው የጋራ ተጠቃሚነትን ለማስፋት፣ የሁለቱን ሀገራት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ለማጠናከር እንዲሁም የኢንቨስትመንት አማራጮችን በማስፋት ዙሪያ መክረዋል፡፡ አቶ አደም ፋራህ የኢትዮ-ቻይና ዘመናትን የተሻገረ ወዳጅነት ይበልጥ ተጠናክሮ መቀጠሉንና የቻይናው ኮሙኒስት ፓርቲ አጋርነትም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን ጠቅሰዋል። ከዚህ በፊት በሁለቱ ፓርቲዎች ስምምነት መሰረት በትምህርት፣ በስልጠና እንዲሁም በተሞክሮና ልምድ ልውውጥ አብሮ መስራት በሚችሉባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ስምምነት መደረጉን አንስተዋል፡፡ በቅርቡ የብልፅግና ፓርቲ ከፍተኛ አመራሮች ተሳታፊ የሆኑበት የልዑካን ቡድን ውጤታማ ቆይታ አድርጎ መመለሱም የዚህ ስምምነት አካል መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ ለልዑካን ቡድኑ ለተደረገው አቀባበልና ስኬታማ የቆይታ ጊዜ ያላቸውን ምስጋና ገልጸዋል። በቀጣይም የፓርቲ ለፓርቲ ግንኙነቶች በመሰል የስልጠናና የልምድ ልውውጥ መርሐ ግብሮች ተጠናክሮ እንዲቀጥል ብልፅግና ፓርቲ ፍላጎቱ እንደሆነ ማብራራታቸውን ከፓርቲው የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡ አምባሳደር ዣዎ ዢዋን በበኩላቸው የብልፅግና ፓርቲ በኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልጽግና ለማረጋገጥ እየሰራቸው ያሉ ውጤታማ ስራዎችን አድንቀዋል፡፡ ኢትዮጵያ የቻይና ጠንካራ ስትራቴጂክ አጋር መሆኗን ጠቅሰው ይህ ግንኙነት በፓርቲ ለፓርቲም ሆነ በመንግስታዊ ወዳጅነት ወደ ተሻለ ደረጃ እንዲያድግ እንደሚሰሩ ገልጸዋል።
ዜጎች በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባትና የተቀራረበ ግንዛቤ እንዲኖራቸው የምሁራን ሚና ከፍተኛ ነው-ዶክተር ከይረዲን ተዘራ
Apr 19, 2024 236
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ ዜጎች በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባትና የተቀራረበ ግንዛቤ እንዲይዙ ምሁራን የላቀ ሚናቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ከይረዲን ተዘራ ገለጹ። የሰላም ሚኒስቴር "ዘመኑን የዋጀ አርበኝነት ለህብረ-ብሔራዊ አንድነት" በሚል መሪ ሃሳብ ሀገር አቀፍ የንቅናቄ መድረክ ያስጀመረ ሲሆን በእለቱ ከዩኒቨርሲቲ ምሁራን ተወካዮች ጋር ውይይት ተካሂዷል። በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የሰላም ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ከይረዲን ተዘራ ከዚህ ቀደም "አድዋን ለዘላቂ ሰላምና ለጠንካራ ሀገረ መንግስት ግንባታ" በሚል መሪ ሃሳብ ከ 40 በላይ የከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር ውይይት መካሔዱን አስታውሰዋል። በመድረኮቹ የጋራ ማንነት ፣ እሴት እና ሀገራዊ ጥቅም ላይ ያተኮሩ ስኬታማ ውይይቶች መደረጋቸውን በማስታወስ ኩነቱ በቀጣይ ለሚካሔዱ የንቅናቄ መድረኮች ትልቅ ግብአት የተገኘበት መሆኑን ተናግረዋል። ምሁራን መሰል ሀሳቦችን በማውረድ፣ በማወያየት እና በማዳበር በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባትና የተቀራረበ ግንዛቤ እንዲኖር ለማስቻል የላቀ ሚና እንዳላቸው ገልጸዋል። "ዘመኑን የዋጀ አርበኝነት ለህብረ-ብሔራዊ አንድነት" በሚል መሪ ሃሳብ ይፋ የተደረገው ንቅናቄም በተመሳሳይ መልኩ የሚተገበር መሆኑን ተናግረዋል። በሁሉም ዘርፍ ለሀገር ልማትና ብሄራዊ ጥቅም ታማኝ ሆኖ መስራት ከዜጎች የሚጠበቅ ተግባር በመሆኑ በተለይም ምሁራን በዚህ ረገድ ብዙ መስራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። በዩኒቨርሲቲዎች የተቋቋሙ ፎረሞች በዚህ ረገድ ከፍ ያሉ ሀሳቦችን በማንሳት ውይይት በማድረግ ለንቅናቄው ስኬት የሚጠበቅባቸውን ሃላፊነት እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል። የውይይቱ ተሳታፊ ምሁራን በበኩላቸው ለውይይቱ የሚረዱ አስፈላጊ የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን እያከናወኑ መሆናቸውን ገልጸዋል። በሀገሪቱ ያለው የውይይት ባህል እንዲዳብርና በመነጋገር የሚያምን ትውልድ እንዲፈጠር የሚጠበቅባቸውን ሃላፊነት እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። በዚህ ረገድ ምሁራን ግንባር ቀደም ሚና መጫወት እንዳለባቸው ገልጸው ውይይቶቹ እንደ ከዚህ ቀደሞቹ የተሳኩ እንዲሆኑ በትኩረት እንደሚሰሩ ተናግረዋል።
የሽግግር  ፍትህ ፖሊሲ እና የፌዴራል አስተዳደር ሥነ ስርአት አዋጅ የዜጎች ሰብዓዊና ፍትሕ የማግኘት መብቶች እንዲከበሩ የሚያስችሉ ናቸው- አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ
Apr 19, 2024 201
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ እና የፌዴራል አስተዳደር ሥነ ስርአት አዋጅ የዜጎችን ሰብዓዊና ፍትሕ የማግኘት መብት የሚያስከብሩ መሆናቸውን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ተናገሩ። በፌደራል አስተዳደር ስነ-ስርዓት አዋጅ እና በሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ትግበራ ላይ ያተኮረ ውይይት መድረክ ተካሂዷል። የሕዝብ ተወካየች ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊዎች፣ የዴሞክራሲ ተቋማት የስራ ሃላፊዎችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በውውይቱ ተሳትፈዋል። አፈ ጉባዔ ታገሰ ጫፎ በዚህ ወቅት እንዳሉት በኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች አግባብ ባለው፣ በተቀናጀና አሳታፊ በሆነ መልኩ መፍትሄ ሳይሰጣቸው ቆይተዋል። በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ሽግግር እና ዘላቂ ሰላም ለማረጋገጥ የሽግግር ፍትህ ሂደት መተግበር "ጠቃሚ ብቻ ሳይሆን እጅግ አስፈላጊ መሆኑን ሀገራዊ አውዱ ያመላክታል" ብለዋል። የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲው ተጎጂዎችን ማዕከል ያደረገ፣ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች መርሆችና ድንጋጌዎችን ያከበረ፣ የሀገሪቱን ፖለቲካና ማህበራዊ ዐውዶችን ባገናዘበ መልኩ መዘጋጀቱን አንስተዋል። ፖሊሲው በገለልተኛ ባለሙያዎች ቡድን የተዘጋጀ፣ በባለድርሻ አካላትና ምሁራን ውይይት ተደርጎበት የጸደቀ መሆኑን ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ለማረጋገጥ የነበሩ ቁስሎችን ሊያሽር፣ ቁርሾዎችን ሊያስቀር የሚያስችል የመፍትሔ ሀሳቦችን ይዞ መዘጋጀቱን ገልጸዋል። መንግስት የዜጎችን ፍትህ የማግኘት መብት እንዲሁም የህግ የበላይነት እንደረጋገጥና መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን የሚያስችል የፌዴራል አስተዳድር ሥነ ስርዓት አዋጅ ተግባራዊ ማድረጉንም ተናግረዋል። ሁለቱ የሕግ ማዕቀፎች የዜጎች ሰብዓዊ መብት እና ፍትህ የማግኘት መብት እንዲረጋገጥ ካመቻቸው ጉልህ ፋይዳ አኳያ ፍትህ ሚኒስቴርን ጨምሮ ባለድርሻ አካላት ለተፈጻሚነቱ እንዲሰሩ አሳስበዋል። የፍትህ ሚኒስትሩ ዶክተር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ በበኩላቸው ዘመናዊ የመንግስት ስርዓት ከተጀመረ ረጅም ጊዜ ቢሆነውም የህግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ የተለያዩ ጉድለቶችና የዘፈቀደ ውሳኔዎች ይስተዋሉ ነበር ብለዋል። በዚህም የመልካም አስተዳደር ችግር መስተዋሉን ገልጸው፤ እንደዚህ አይነት የህግ ማዕቀፎች ለብዙ ችግሮች መፍትሄ እንደሚሆኑ ተናግረዋል። የህግ ማዕቀፎችን ማዘጋጀት ወሳኝ እርምጃ ቢሆንም ለተግበራዊነታቸው ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥር እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል። የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ በጥንቃቄና አሳታፊነቱን ተጠበቆ የተዘጋጀ፣ የላቀ ሀገራዊ ጠቀሜታ ያለው ፖሊሲ በመሆኑ ለትግበራው የባለድርሻ አካላትን ትብብርና ክትትል እንደሚጠይቅ ገልጸዋል። በዚህም በቀጣይ የማስፈጸሚያ የሕግ ማዕቀፍ በማውጣት የሽግግፍ ፍትሕ ፖሊሲውን ተግባራዊ ማድረግ እንደሚገባ ገልጸዋል።    
የተሳታፊ ልየታ በተከናወነባቸው አካባቢዎች የአጀንዳ ማሰባሰቢያ መድረኮችን ለመጀመር የሚያስችሉ ዝግጅቶች ተጠናቀዋል-- የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን
Apr 19, 2024 310
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ ለአገራዊ ምክክሩ የተሳታፊ ልየታ በተከናወነባቸው አካባቢዎች የአጀንዳ ማሰባሰቢያ ህዝባዊ መድረኮች ለመጀመር የሚያስችሉ ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውን የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ገለጸ፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን እንደ ሀገር በሚስተዋሉ ችግሮች ላይ በመወያየት በዘላቂነት ለመፍታት፣ ብሔራዊ መግባባትና ሀገራዊ አንድነት ለመፍጠር በአዋጅ የተቋቋመ ገለልተኛ ተቋም ነው፡፡ ኮሚሽኑ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አዋጅ ቁጥር 1265/2014 ፀድቆ ወደ ሥራ ገብቷል፡፡ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ቃል አቀባይ ጥበቡ ታደሰ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ከሚሽኑ ኃላፊነቱን ተረክቦ ወደ ሥራ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ ለምክክሩ ስኬት የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን ሲያሰባስብ ቆይቷል፡፡ ባለፉት ሁለት ዓመታት ለምክክሩ ውጤታማነት አስፈላጊ በሆኑ የተሳታፊ ልየታ መድረኮች መካሄዳቸውን ገልጸዋል፡፡ በዚህም ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችና የህዝብ አደረጃጀቶች ጋር ሰፊ የውይይት መድረኮች በማዘጋጀት ተጨባጭ ውጤት ተገኝቷል ብለዋል፡፡ በተሳታፊ ልየታው የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች፣ ፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ሲቪክ ማህበራት፣ የኃይማኖት ተቋማት፣ የዳያስፖራና የተለያዩ ትምህርት ተቋማት፣ በዕድሜና ጾታ ጭምር ተካተዋል ብለዋል። የተሳታፊ ልየታ ባልተከናወነባቸው አካባቢዎች ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ስራዎችን ለማጠናቀቅ እንደሚሰራም ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም ኮሚሽኑ ምክክር የሚደረግባቸው የአጀንዳ ሀሳቦችን ከጥናቶች፣ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችና ከህዝባዊ መድረኮች የማሰባሰብ ስልጣን እንደተሰጠው ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም የተሳታፊ ልየታ በተደረገባቸው ክልሎች የአጀንዳ ሀሳብ ለማሰባሰብ የሚያስችሉ ህዝባዊ መድረኮችን ለመጀመር የሚያስችሉ ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውን አብራርተዋል፡፡ ምክክር ኮሚሽኑ በሀገሪቱ ከሚገኙ ከአንድ ሺህ 300 ወረዳዎችና ከተማ አስተዳደሮች የሚሳተፉ ተሳታፊዎች ጋር የአጀንዳ ማሰባሰቢያ መድረኮችን ያዘጋጃል ብለዋል፡፡  
ወጣቶች ሰላማቸውን በማስጠበቅ ሁለንተናዊ ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የጀመሩትን ጥረት ማጠናከር አለባቸው - አቶ እንዳሻው ጣሰው
Apr 19, 2024 207
ወልቂጤ ፤ ሚያዝያ 11/ 2016(ኢዜአ)፦ወጣቶች የአካባቢያቸውን ሰላም በማስጠበቅ የልማትና የመልካም አስተዳደር ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የጀመሩትን ጥረት ማጠናከር እንዳለባቸው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳደር አቶ እንዳሻው ጣሰው ገለጹ። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ ከጉራጌ ዞን የተለያዩ መዋቅሮች ከተወጣጡ ወጣቶች ጋር በወጣቶች የልማትና የመልካም አስተዳደር ተሳትፎና ተጠቃሚነት ላይ እየተወያዩ ነው። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት የክልሉ ወጣቶች የአካባቢያቸውን ሰላም በማስጠበቅ የልማትና መልካም አስተዳደር ተሳትፎና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የጀመሯቸውን አበረታች ሥራዎች ማጠናከር አለባቸው። ሰላም ለሁሉም መሠረት በመሆኑ ሰላማቸውን በቅንጅት ከማጠናከር ባለፈ በአካባቢያቸው የልማት ሥራዎች ተሳታፊና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ ጠንክረው መስራት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ወጣቱ ትውልድ በመደመር ዕሳቤ ለውይይትና ለውስጥ ሰላሙ ትኩረት ሰጥቶ መንቀሳቀስና ገዥ ትርክቶችን አጉልቶ ማውጣት እንዳለበትም ተናግረዋል። አቶ እንዳሻው እንዳሉት ወጣቱ አዳዲስ እሳቤዎችን እያፈለቀና ባለው ላይ እየጨመረ የብልጽግና ጉዞን ለማፍጠን የሚደረገውን ጥረት ማገዝ አለበት። በተለይ የሚያግባቡ እና የሚያስተሳስሩ ጉዳዮች አጉልቶ በማውጣትና የወል ትርክቶችን በማጠናከር የተጀመረውን የብልጽግና ጉዞ ለማፋጠን መረባረብ ይኖርበታል። ልማትን ለማጠናከር ዘላቂ ሰላምና የህዝቦች አንድነት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት አቶ እንደሻው፣ በክልሉ ሁለንተናዊ ልማትን ለማፋጠን እየተሰሩ ያሉ ሥራዎች ውጤታማ እንዲሆኑ ወጣቶች የበኩላቸውን እገዛ እንዲያደርጉ አሳስበዋል።      
ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ የተሽከርካሪ መገጣጠሚያ እና ማምረቻ ኢንዱስትሪ ግንባታ የመሰረተ ድንጋይ አስቀምጡ
Apr 19, 2024 229
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/ 2016(ኢዜአ)፦የጦር ሃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ የተሽከርካሪ መገጣጠሚያ እና ማምረቻ ኢንዱስትሪ ግንባታ የመሰረተ ድንጋይ አስቀምጡ። የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ ከተመሰረተ በርካታ ዓመታትን ያሳለፈው የመከላከያ ኢንዱስትሪ ዘመኑ ከደረሰበት የዕድገት ደረጃ ለማድረስ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ ገልፀው፣ የፋብሪካው ግንባታ ለሀገርና ለተቋሙ የሚሰጠው ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑን ተናግረዋል።   ኢንዱስትሪው በአዲስ መልኩ ከተደራጀ በኋላ በተሰሩት ስራዎች ከኪሳራ ወደ ትርፋማነት መሸጋገሩን የገለፁት ጠቅላይ ኤታማዦር ሹሙ የኮርፖሬሽኑ አመራርና አባላቶች ለነበራቸው ቁርጠኝነት ምስጋናቸውን አቅርበዋል። ተቋሙ የራሱን ገቢ በማመንጨት ለሰራዊቱ መሰረታዊ ጥቅም ለማሟላት አቅጣጫ ተቀምጦ እየተሰራ መሆኑንም ተናግረዋል። ጠቅላይ ኤታማዦር ሹሙ የሰራዊቱን የመኖሪያ ቤት ባለቤት ለማድረግና ተጠቃሚነቱን ለማረጋገጥ በኢንዱስትሪ ፤ በግብርና ፣ በማዕድንና በመሰረተ ልማት ዝርጋታ ላይ ከተሰማሩ ባለሀብቶች ጋር ለመስራት የተቀመጠው አቅጣጫ ማሳያ መሆኑን ጠቁመዋል።   የመከላከያ ኢንጅነሪንግ ኢንዱስትሪ ኮርፖሬሽን ዋና ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ሀይለማርያም የመከላከያ የተሽከርካሪ መገጣጠሚያ እና ማምረቻ ኢንዱስትሪ ከሽርሽር ኢንቨስትመንት ግሩፕ ጋር በመሆን የሚገነባው መሆኑን ተናግረዋል። ኢንዱስትሪው በሰላሳ ሄክታር መሬት ላይ የሚያርፍና በአንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ መታቀዱንም ዋና ዳይሬክተሩ ገልፀዋል። አለም አቀፍ ስታንዳርዳቸውን ያሟሉ ወታደራዊ ተሽከርካሪዎችን ከመገጣጠምና ከማምረት ባለፈ በቀጣይ ፕሮጀክቱን የማስፋፋት ዕቅድ እንዳላቸው የገለፁት ዳይሬክተሩ ለፕሮጀክቱ ስኬት ያልተቋረጠ ድጋፍና ክትትል እንደሚደረግም ጠቁመዋል። በዝግጅቱ ላይ የመከላከያ ሚንስቴር ዲኤታ አቶ ቶማስ ቶት ፣የቢሾፍቱ ከተማ ከንቲባ አቶ አለማየሁ አሰፋ ና ወታደራዊ አታሼዎች እንዲሁም ከፍተኛ የሰራዊቱ አመራሮች መገኘታቸውን የመከላከያ ሠራዊት መረጃ ያመለክታል።
ኮሚሽኑ በመሰረታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ሀገራዊ መግባባት እንዲፈጠር ሀላፊነቱን እየተወጣ ነው---ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ
Apr 19, 2024 211
ሻሸመኔ፤ ሚያዚያ 11/2016 (ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በመሰረታዊ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ሀገራዊ መግባባት እንዲፈጠር ሀላፊነቱን በአግባቡ ለመወጣት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ ገለጹ። በኦሮሚያ ክልል በዞን፣ በወረዳና በከተማ አስተዳደር ደረጃ በምክክር ሂደቱ የሚሳተፉ የህብረተሰብ ተወካዮች ልየታ የማጠቃለያ መድረክ በሻሸመኔ ከተማ እየተካሄደ ነው። በመርሀ ግብሩ ላይ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ እና ምክትል ዋና ኮሚሽነር ዶክተር ሒሩት ገብረስላሴ ተገኝተዋል። ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን በመድረኩ እንደገለጹት ኮሚሽኑ እጅግ መሰረታዊ በሆኑ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ሀገራዊ መግባባት እንዲፈጠር የተጣለበትን ሀላፊነት በአግባቡ ለመወጣት እየሰራ ነው። የተጣለበትን ተልዕኮ ለመወጣት ገለልተኛ ተቋማትና ተባባሪ አካላትን ጭምር በማሳተፍ እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ገልጸዋል። በእዚህም ኮሚሽኑ የምክክር አጀንዳዎችን ከህብረተሰቡ ጋር የመቅረፅ፣ አጀንዳዎቹ ምክክር እንዲደረግባቸው የማመቻቸት እና ምክክሮችና ውይይቶችን የማሳለጥ ሃላፊነቱን በአግባቡ ለመወጣት እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ነው ፕሮፌሰር መስፍን ያስታወቁት በኦሮሚያ ክልል የተሳታፊ ልየታ ሂደቱ እስኪጠናቀቅ ድረስ የክልሉ መንግስት፣ የሻሸመኔ ከተማ አስተዳደር፣ ተባባሪ አካላትና ተሳታፊዎች ላደረጉት አስተዋጾም በኮሚሽኑ ሥም ምስጋና አቅርበዋል በሻሸመኔ ከተማ እየተካሄደ ባለው የማጠቃለያ የማህበረሰብ ተወካዮች ልየታ መድረክ ከምስራቅ ቦረና ዞን የነገሌ ከተማ አስተዳደርን ጨምሮ ከዋጭሌ፣ ዳሳ፣ አሬሮ፣ መደወላቡ፣ ጉሮዶላ እና ሊበን ወረዳዎች የተውጣጡ 500 የሚጠጉ የህብረተሰብ ተወካዮች እየተሳተፉ ይገኛሉ። በመድረኩ የሀገራዊ ምክክር ምንነትና አስፈላጊነት እንዲሁም የአመራረጥ ሂደቱን በማስመልከት ለተሳታፊዎች ገለጻ ተደርጓል። የኢትዮጵያ ሃገራዊ የምክክር ኮሚሽን ወደስራ ከገባ ጀምሮ በክልሎችና በከተማ መስተዳደሮች በርካታ የቅድመ ዝግጅት እና የተሳታፊ ልየታ ሥራዎችን አከናውኗል። በቀጣይም ኮሚሽኑ የተሳታፊዎች ልየታ ባልተከናወነባቸው ክልሎች ልየታ በማድረግ አጀንዳዎችን በህዝባዊ ውይይቶች በማሰባሰብ ምክክሮች እንዲካሄዱ ያድርጋል። በእዚህም አለመግባባቶችን ለመፍታት የሚያግዙ የሀገር ሽማግሌዎችንና በማህበሩሰቡ መካከል ተፅዕኖ ፈጣሪ የሆኑትን የመለየትና ተቀራርቦ የመወያየት ስራዎችን እንደሚያከናወኑ ታውቋል። በምክክር ሂደቱ ውጤታማና በሃገሪቱ የተሻለ የሰላምና የፖለቲካ መደላድል እንዲፈጠር ሁሉም የበኩሉን አስተዋጾ ማበርከት እንዳለበት ኮሚሽኑ በተለያዩ ጊዜያት ጥሪ ማቅረቡም የሚታወስ ነው።        
የመካከለኛው ምሥራቅ ቀጣና ችግሮች እንዲፈቱ ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በትብብር ትሰራለች- ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር
Apr 19, 2024 180
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የመካከለኛው ምሥራቅ ቀጣና ችግሮች እንዲፈቱ ከወዳጅ አገራትና ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በትብብር እንደምትሰራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገለፀ። በሰላም ዕጦት ውስጥ ያሉ የአፍሪካ ቀንድ አገራት ሰላምና መረጋጋት እንዲረጋገጥም አበክራ እንደምትሰራም ገልጿል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ፣ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ተለዋዋጭ በሆነው ዓለም ኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅሟንና ፍላጎቷን መሰረት ያደረገ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲን ታራምዳለች። 'የኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ አልፋና ኦሜጋ ብሔራዊ ጥቅም ነው' ያሉት አምባሳደሩ፣ ዲፕሎማሲው ከሀገር ሰላም፣ ልማትና ደህንነት አኳያ ታሳቢ ያደረገ መሆኑን ነው ያነሱት። በዚህም በተለዋዋጩ ዓለም ውስጥ ኢትዮጵያ የምትወስዳቸው አቋሞች ከራሷ ብሔራዊ ጥቅም አኳያ መዝና እንደሆነ አንስተዋል። ኢትዮጵያ ከመካከለኛው ምስራቅ ጋር ካላት መልክዓ ምድራዊና የህዝብ ለህዝብ ትስስር አኳያ የቀጣናው ቀውስና መረበሽ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅም ቀጥተኛ አንድምታ እንዳለው ተናግረዋል። በዚህም የቀጣናው ችግሮች እንዲፈቱና ኢትዮጵያ ብሄራዊ ጥቅሞች እንዲከበሩ ከአጋር አገራት እና ዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በትብብር እንደምትሰራ ገልፀዋል። በተመሳሳይ ኢትዮጵያ በውጭ ጉዳይ ፖሊሲዋ ለጎረቤት ሀገራት ቀዳሚ ትኩረት እንደምትሰጥ ገልፀው፣ በተለይም ጎረቤት አገራት ቀውስ ለኢትዮጵያ እንደሚተርፍ ተናግረዋል። በዚህም በሰላም ዕጦት ለሚቸገሩ ጎረቤት አገራት ሰላምና መረጋጋት እንዲፈጠር በታሪክ የነበራትን የሰላም ማስከበር ሚና አጠናክራ ትቀጥላለች ብለዋል። ከሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ባሻገርም ኢትዮጵያ በቀጣናው ኢኮኖሚያዊ ትስስር ለመፍጠር የሚያስችል የዲፕሎማሲ ስራዎችን ማከናወኗን ገልጸዋል። የባሕር በርን ጨምሮ ፀጋዎችን አልምቶ በጋራ በመጠቀምና የመሰረተ ልማትና ንግድ ትስስር በማጎልበት የጋራ ዕድገትን ማረጋገጥና የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ማጠናከር የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል።    
የጋምቤላ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ለስምንት አዳዲስ የአመራር አባላት ሹመቶችን ሰጠ
Apr 19, 2024 76
ጋምቤላ፤ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ የጋምቤላ ክልላዊ መንግስት ከአመራር የማስፈፀም አቅም ጋር ተያይዘው የሚነሱ ችግሮችን ከምንጩ ለመፍታት የአመራር ሽግሽግ ማድረጉን አስታወቀ። የክልሉ መንግስት ዛሬ አዳዲስ ሹመቶችን የሰጠው በህዝቡ ለሚነሱ የሰላም፣ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት በማሰብ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ኡሞድ ኡጁሉ ገልጸዋል። በዚህም መሰረት፦ 1 አቶ ባጓል ጆክ_ የክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ 2. አቶ ቻም ኡቦንግ_ የክልሉ ፍትህ ቢሮ ኃላፊ 3. አቶ ቱት ጆክ_ የክልሉ ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ 4. ዶክተር ቾል ኬድ_ የክልሉ ገጠር መንገዶች ባለስልጣን ዋና ዳይሬክተር 5. አቶ ቾል ማቢየል_ የክልሉ ብዙሃን መገናኛ አገልግሎት ኃላፊ 6. አቶ ጉባይ ጆክ_ የክልሉ ጤናና ጤና ነክ ክትትልና ቁጥጥር አገልግሎት ኃላፊ 7. አቶ ላም ታንግ _ የክልሉ ስራና ክህሎት ቢሮ የስራ ዘርፍ ምክትል ቢሮ ኃላፊ 8. አቶ ጋትዊች ቢየል_ የክልሉ ውሃ ስራዎች ኮንስትራክሽን ምክትል ስራ አስኪያጅ በመሆን ተሹመዋል። ሹመት የተሰጣቸው የአመራር አባላት በትምህርት ዝግጅታቸው የበቁ፣ በእኩልነት አመለካከት የሚያምኑ፣ በስራ ልምዳቸውና በአፈፃፀማቸው ውጤታማ የሆኑ መሆናቸውንም ርዕሰ መስተዳድሩ አስታውቀዋል። በተጨማሪም የመንግስት ተልዕኮ በአግባቡ ተቀብለው የሚፈፅሙና የሚያስፈፅሙ መሆናቸው ታምኖበታል ሲሉም ተናግረዋል።    
ኮሚሽኑ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሀብት ማሳወቅና ምዝገባ እንዲሁም የሙስና መረጃ ትንተናና ጥቆማ መቀበል ረገድ የተሻለ ስራ መስራቱን ገለጸ
Apr 19, 2024 86
አዳማ ፤ ሚያዝያ 11/2016(ኢዜአ)፦ የፌዴራል ስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ባለፉት ዘጠኝ ወራት በሀብት ማሳወቅና ምዝገባ እንዲሁም የሙስና መረጃ ትንተናና ጥቆማ መቀበል ረገድ የተሻለ ስራ መስራቱን ገለጸ። የሁሉም ክልሎች የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽነሮች የተሳተፉበት በሙስና ተጋላጭነት ዙሪያ የምክክር መድረክ በአዳማ በመካሄድ ላይ ይገኛል። በኮሚሽኑ የስነ-ምግባር ግንባታ ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር አቶ ወዶ አጦ በዚሁ ወቅት እንደገለፁት በሀብት ማሳወቅና ምዝገባ እንዲሁም የሙስና መረጃ ትንተናና ጥቆማ መቀበል ላይ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተሻለ ሥራ ተሰርቷል። በተለይም በአስቸኳይ ሙስና መከላከል ስራና የሙስና ስጋት ተጋላጭነት ጥናት በትኩረት መከናወኑን ጠቅሰው፣ በዚህም በርካታ የህዝብና የመንግስት ሀብትን ከምዝበራ መታደግ ተችሏል ብለዋል። በተጨማሪም የክልሎችን የስነ-ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽነሮች አቅም የመገንባት፣ ተቋማዊ የሙስና መከላከል አቅም ግንባታና የሙስና መከላከል ሪፎርም ላይ ዘርፈ ብዙ ተግባራት መከናወናቸውንም አስታውቀዋል። በስነ-ምግባር ግንባታና በሙስና መከላከል ስራ የተሻለ ውጤት መገኘቱን ገልጸው፤ መድረኩ የክልሎች የፀረ ሙስና ኮሚሽን ልምድ የሚለዋወጡበትና የሚማማሩበት መሆኑንም አመልክተዋል።   በኮሚሽኑ የሙስና መከላከል ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር አቶ እሸቴ አስፋው በበኩላቸው ኮሚሽኑ በ25 ዘርፎች ላይ የሙስና ተጋላጭነት ጥናት ለማድረግ አቅዶ በ19ኙ ላይ ማከናወኑን አስታውቀዋል። ቀሪዎቹ ዘርፎች ላይ የሙስና ተጋላጭነት ጥናት እየተካሄደ መሆኑን በማከል። የሙስና ትግሉ የታለመለትን ግብ እንዲያሳካ መብቱን በገንዘብ የማይገዛና ሙስናን መሸከም የማይችል ማህበረሰብ መገንባት ወሳኝ ሚና አለው ብለዋል። የሙስና መከላከልና የዘርፉን ህግ ማስፈፀም ላይ የፖለቲካ አመራሩና ኮሚሽኑ ተቀናጅተው መስራት እንደሚገባቸውም ምክትል ኮሚሽነሩ ተናግረዋል። በተጨማሪም የአገልግሎት ሰጪ ተቋማትን የአሰራር ስርዓት ማዘመንና ለህዝብ የሚሰጠውን አገልግሎት በቴክኖሎጂ ማስደገፍ ለፀረ ሙስና ትግል ስኬት ቁልፍ አጋዥ መሆኑን ገልጸዋል። የሙስናና ብልሹ አሰራር መንስዔን በጥናት በመለየት አስቸኳይና መደበኛ የሙስና መከላከል ስራዎችን ማጠናከር ከሁላችንም የሚጠበቅ ቀዳሚ ተግባር ነው ሲሉም አሳስበዋል። በየደረጃው ያሉ የፌዴራልና የክልል የስነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽኖች የአሰራር ስርዓታቸውን በቴክኖሎጂ አስደግፈው መምራት እንደሚገባቸው በማጽናት። በግዥ፣ በግንባታ፣ በአገልግሎት አሰጣጥና በፍትህና በመሬት ላይ የሚፈፀም ሙስናን ለመከላከል የጋራ ዕቅድ ሊኖረን ይገባል ነው ያሉት። የመሬት ሀብቱን ወደ ዘመናዊ የመሬት አስተዳደር ካዳስተር ማስገባትና በቴክኖሎጂ በመምራት በዘርፉ የሚፈፀም ሙስናና ምዝበራ መግታት እንደሚገባም ምክትል ኮሚሽነሩ አስገንዝበዋል።    
በአፍሪካ ቀንድና በቀጣናዊ ደህንነት ላይ ያተኮረ ውይይት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው
Apr 19, 2024 167
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016 (ኢዜአ)፦ በአፍሪካ ቀንድና ቀጣናዊ ደህንነት ላይ ያተኮረ ውይይት በአዲስ አበባ በመካሄድ ላይ ነው። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ያዘጋጀው ውይይት “ለውስብስብ ጉዳዮች አማራጭ መንገዶችን በመፈለግ፤ በአፍሪካ ቀንድ ቀጣናዊ ደህንነትን ማረጋገጥ” በሚል መሪ ሀሳብ ነው እየተካሔደ ያለው። በውይይቱ ላይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ፣ የውጭ ጉዳይ ኢኒስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ጃፋር በድሩና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።   በቀጣናው የደህንነት ምህዳር ላይ እየታዩ ያሉ ለውጦችና አንድምታቸው፣ የውጭ ኃይሎች በቀጣናው ደህንነት ላይ ያላቸው ሚና ላይ ያተኮሩ የመነሻ ጽሑፎች ቀርበው ውይይቶች እንደሚካሔድባቸውም ተገልጿል። ጠንካራና የተሳሰረ ቀጣና ግንባታ ለዘላቂ ሰላምና መልካም እድሎች ያለውን ሚና የተመለከቱም ጽሁፎች ቀርበው የፓናል ውይይቶች እንደሚደረግባቸውም ገልጸዋል። በዛሬው እለት የሚካሔደው ውይይት የአፍሪካ ቀንድን አስመልክቶ እየተካሄዱ ያሉ ውይይቶች ቀጣይ አካል መሆኑ ተገልጿል። እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ሐምሌ 2023 መሰል ውይይት በጅቡቲ መካሄዱ የሚታወስ ነው። የውጭ ጉዳይ ኢኒስቲትዩት በውጭ ግንኙነትና ዲፕሎማሲ፣ በሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ጥናትና ምርምር በማከናወን አገራዊ፣ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፋዊ የምክከር መድረኮችን በማዘጋጀት ለፖሊሲ አማራጭ ምክረ ሀሳቦችን የሚያቀርብ ተቋም ነው። በተጨማሪም ኢኒስቲትዩቱ ለዲፕሎማቶችና ለባለድርሻ አካላት ስልጠናዎችን እየሰጠ ይገኛል።        
የሽግግር  ፍትህ ፖሊሲ በኢትዮጵያ  ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት ማስፈን የሚያስችል መፍትሄ ይዞ ተዘጋጅቷል- አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ 
Apr 19, 2024 111
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 11/2016(ኢዜአ)፦ የሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ለዘመናት ሲንከባለሉ ለመጡ ቁርሾች መፍትሄ በመስጠት ዘላቂ ሰላም ና መረጋጋት ማስፈን በሚያስችል አግባብ መዘጋጀቱን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ተናገሩ። አፈ ጉባኤው ይህን የተናገሩት በፌደራል አስተዳደር ስነ-ስርዓት አዋጅ እና በሽግግር ፍትህ ፖሊሲ ላይ በተዘጋጀው የውይይት መድረክ ላይ ነው። በኢትዮጵያ በተለያየ ጊዜ የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች አግባብ ባለው፣ ሁለንተናዊ፣ የተቀናጀና አሳታፊ በሆነ መልኩ መፍትሄ ሳይሰጣቸው መቆየታቸውን አንስተዋል። በመሆኑም ዘላቂ ሰላም ማረጋገጥ እንዲቻል የሽግግር ፍትህ ሂደት መተግበር "ጠቃሚ ብቻ ሳይሆን እጅግ አስፈላጊ መሆኑን አገራዊ አውዱ ያመላክታል" ብለዋል። ከዚህ አኳያ አሳታፊ፣ ተጎጂዎችን ማዕከል ያደረገ፣ ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶችና መርሆችና ድንጋጌዎችን ያከበረ፣ የአገሪቱን ፖለቲካና ማህበራዊ አውዶችን መሰረት ያደረገ የሽግግር ፍትህ ሂደት መቀመርና በግልጽ የፖሊሲ ማዕቀፍ እንዲመራ ለማድረግ ፖሊሲው መዘጋጀቱን ገልጸዋል።   ፖሊሲው በጥናትና ምርምር ላይ የቆዩ ገለልተኛ የሙያተኞች ቡድን የተዘጋጀ ፣ የተለያዩ ባለድርሻ አካላትና ምሁራን ውይይት አድርገውበት በሚኒስትሮች ምክር ቤት መጽደቁን አስታውሰዋል። በኢትዮጵያ መግባባትን ወደፊት ለማስቀጠል ቁስሎችን ሊፈውስ እና ቁርሾዎችን ሊያስቀር የሚያስችሉ የመፍትሔ ሀሳቦችን ይዞ መዘጋጀቱን ተናግረዋል። በሌላ በኩል የዜጎችን የአሰተዳደር ፍትህን ለማረጋገጥ ስራ ላይ የዋለው የአስተዳደር ስነ-ስርአት አዋጅ ላይ የሚነሱ ክፍተቶች ማረም ላይ በቀጣይ በትኩረት አንዲሰራ አሳስበዋል፡፡ በውይይት መድረኩ የዴሞክራሲ ተቋማትና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎች ተገኝተዋል።  
በክልሉ አንድነትና አብሮነትን በማጠናከር ዘላቂ ሰላምና ልማት ለማረጋገጥ መንግስት ከህብረተሰቡ ጋር በትኩረት እየሰራ ነው - ርዕሰ መስተዳድር ኡሞድ ኡጁሉ
Apr 18, 2024 340
ጋምቤላ፤ ሚያዚያ 10/2016(ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል አንድነትና አብሮነትን በማጠናከር ዘላቂ ሰላም ለማስፈንና ልማትን ለማረጋገጥ ከህብረተሰቡ ጋር እያከናወነ ያለውን ተግባር አጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኡሞድ ኡጁሉ ገለፁ። ርዕሰ መስተዳድሩ ይህን ያሉት በክልሉ ወቅታዊ የፀጥታ ጉዳዮች ዙሪያ ከአኝዋሃ ዞን ከተውጣጡ የህብረተሰብ ተወካዮች ጋር ዛሬ በጎግ ወረዳ በመከሩበት ወቅት ነው።   ርዕሰ መስተዳድሩ አቶ ኡሞድ እንዳሉት፤ የክልሉ መንግስት የህዝቡን አንድነትና አብሮነት በማጠናከር ለክልሉ ዘላቂ ሰላምና ልማት በትኩረት እየሰራ ይገኛል። በክልሉ በዘላቂነት ሰላም ለማስፈን መንግስት ለሚያደርገው ጥረት የማህበረሰቡ እገዛና ትብብር ተጠናክሮ ሊቀጥል እንደሚገባም ተናግረዋል። የህዝቡን ህይወት እንዲቀይሩ ታቅደው የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን ለማሳካት በዋናነት በየአካባቢው የተረጋጋ ሰላም ማስፈን አስፈላጊ መሆኑንም ገልፀዋል። በህዝቦች መካከል ያለውን ተከባብሮና ተቻችሎ የመኖር እሴቶች ይበልጥ እንዲጠናከሩ የጋራ ጥረት አስፈላጊ መሆኑንም ተናግረዋል። የክልሉን ሰላም በዘላቂነት በማፅናት ለተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች መሳካት የህዝቡ ድርሻ ከፍተኛ ነው ያሉት ደግሞ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ቴንኩዌይ ጆክ ናቸው።   በተለይም ከለውጡ ወዲህ በክልሉ ሰፍኖ የቆየውን ሰላም ለማደፍረስ የሚሞክሩ አካላትን በህግ ለመጠየቅ መንግስት እያደረገ ላለው ጥረት ህዝቡ ተባባሪነቱን ማጠናከር እንደሚገባው ገልጸዋል። የክልሉ መንግስት አሁን ላይ የጀመራቸውና ማህበረሰቡን ያሳተፉ የሰላም ግንባታ ስራዎች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። ከውይይቱ ተሳታፊዎች መካከል ወይዘሮ አሪያት ኡታንግ በሰጡት አስተያየት፤ የህዝቡን ሰላም በሚያውኩ አካላት ላይ መንግስት የሚወስደውን ህጋዊ እርምጃ ማጠናከር አለበት። የህግ የበላይነትን ለማረጋገጥ መንግስት ለሚያደርገው ጥረት ሁሉ አስፈላጊውን ትብብር እንደሚያደርጉም ገልፀዋል። ክልሉ ለሚያከናውናቸው የሰላም ግንባታ ስራዎች ስኬታማነት ከመንግስት ጎን በመሆን የበኩላቸውን ሚና ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን የገለፁት ደግሞ ሌላው አስተያየት ሰጪ አቶ ኡቶው ኡዋር ናቸው። መንግስት ወንጀለኞችን በህግ ተጠያቂ ለማድረግ አሁን እያሳየ ያለውን ቁርጠኝነት አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ሲሉም ተናግረዋል። በምክክር መድረኩ ላይ የክልል፣ የዞንና የወረዳ ከፍተኛ የአመራር አባላትን ጨምሮ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ ተዋቂ ግለሰቦች እና የህብረተሰቡ ተወካዮች ተሳትፈዋል።
ኢትዮጵያ እና ኖርዌይ ያላቸውን የሁለትዮሽ ግንኙነት የበለጠ አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገለጹ
Apr 18, 2024 175
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 10/2016 (ኢዜአ)፡- የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ በኢትዮጵያ የኖርዌይ አምባሳደር ስቴን ክሪስተንሰን ጋር የሁለቱን አገራት ግንኙነት የበለጠ ማጠናከር በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ተወያይተዋል። በልማት ትብብር፣ በዘላቂ ሰላም ግንባታ፣ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል እና ለመቋቋም በሚከናወኑ ሥራዎች፣ በውኃ ሀብት አስተዳደር እና ድንበር ተሻጋሪ ሀብቶች አጠቃቀም ዙሪያ የሁለቱን አገራት ትብብር ለማጠናከር ምክክር ተደርጓል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ ኖርዌይ የኢትዮጵያ የረዥም ጊዜ አጋር መሆኗን ገልጸው፤ ይህን ግንኙነት ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ መንቀሳቀስ ይገባል ብለዋል። ኖርዌይ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት የልማት ትብብር ተጠናክሮ እንዲቀጥልም አንስተዋል። ሚኒስትር ዴኤታው በውኃ ሀብት አጠቃቀም እና በአየር ንብረት ለውጥ መከላከል ዙሪያ የሁለቱ አገራት ግንኙነት አጠናክሮ ለመቀጠል በኢትዮጵያ በኩል ያለውን ቁርጠኝነት ገልጸዋል። አምባሳደር ስቴን ክሪስተንሰን በበኩላቸው አገራቸው በተለይ ኢትዮጵያ የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል የምታደርገውን ጥረት በደን ልማት ድጋፍ በኩል አጠናክራ ትቀጥላለች ብለዋል። አምባሳደር ስቴን ክሪስተንሰን አገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት በሁሉም ዘርፎች አጠናክራ ትቀጥላለች ብለዋል።
ለኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ስራ ውጤታማነት እንደግፋለን-  የሀገር ሽማግሌዎችና ወጣቶች
Apr 18, 2024 197
ቦንጋ ፤ሚያዚያ 10 /2016 (ኢዜአ)፡- ለኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ስራ ውጤታማነት ከድጋፍ ባሻገር የነቃ ተሳትፎ እንደሚያደርጉ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ቦንጋ ከተማ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የሀገር ሽማግሌዎች እና ወጣቶች ገለጹ። የኮሚሽኑን ምንነትና ዓላማ ላይ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል በቂ ግንዛቤ ኖሮት ተሳትፎ እንዲያደርግ የተጀመረው ስራ መጠናከር እንዳለበት ተመልክቷል። ከአገር ሽማግሌዎች መካከል አቶ በየነ በቀለ፣ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዘመናትን ለተሻገሩና ያለመግባባት ምክንያት ለሆኑ ጉዳዮች መቋጫ መፍትሄ እንዲያገኝ ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ እንደሚገኝ መረዳታቸውን ተናግረዋል። የኮሚሽኑ ስራ ግቡን እንዲመታ ግንዛቤ በመፍጠርና ተሳትፎ በማድረግ እንዲሁም አስፈላጊ በሆነ ሁሉ ድጋፋቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል።   ሀገራችን ለዘመናት ሲንከባለሉ በመጡ ችግሮች ሳቢያ ላለመግባባትና ለተለያዩ ችግሮች ተዳርጋለች ያሉት ደግሞ ሌላኛው የቦንጋ ከተማ የአገር ሽማግሌ አቶ አሰፋ ገብረማሪያም ናቸው። ለዚህ በምክክር ችግር ዘላቂ መፍትሄ እንዲመጣ ምቹ ሁኔታ እየፈጠረ ያለው የኢትዮጵያ አገራዊ የምክክር ኮሚሽን የሚበረታታና ለተፈጻሚነቱ አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ አበረክታለሁ ብለዋል። አለመግባባቶችን መፍታት የምንችለው በራሳችን አቅምና በጋራ ውይይት ነው ሲሉ ገለጸዋል። ለዚህ እያመቻቸ ያለው ኮሚሽኑ ችግሮችን በሶስተኛ ወገን ሳይሆን በቀጥታ ከህብረተሰቡ ጋር በመገናኘት መፍትሔ ለማፈላለግ ወደ ተግባር መግባቱን እንደሚደግፉ ገልጸዋል። ይህን ታሪካዊ እድል በተገቢው በመጠቀም በሰለጠነ አካሄድ በጋራ ተወያይቶ ዘላቂ መፍትሄ ማበጀት እንደሚያስፈልግም አቶ አሰፋ አመልክተዋል። በዚህም ሰላሟ የተጠበቀ፣ አንድነቷ የጠነከረ እና ለሁሉም ምቹ የሆነች ኢትዮጵያን መፍጠር ላይ በጋራ መረባረብ ይገባናል ብለዋል። ለኮሚሽኑ ስራ መሳካት የሁሉም ህብረተሰብ የነቃ ተሳትፎና ድጋፍ ወሳኝ መሆኑን ያነሱት የአገር ሽማግሌዎቹ፣ የሚጠበቅባቸውን ድጋፍና ተሳትፎ እንደሚያደርጉም አስታውቀዋል።   የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ የተቋቋመበትን ዓላማ ከግብ እንዲያደርስ እንደ የነገ ሀገር ተረካቢ ወጣት ንቁ ተሳታፊ በመሆን አስተዋጽኦ ለማድረግ ዝግጁ ነኝ ያለው ደግሞ ወጣት ዳንኤል መኩሪያ ነው። ወጣቶች ከምንም በላይ ስለሀገር ሰላም፣ አንድነትና ልማት ማሰብ ያለባቸው ጊዜ አሁን ነው ያለው ወጣቱ፣ በተለይ ሀገራዊ አንድነትና ሰላም እንዲሰፍን በምክንያታዊነት ከኮሚሽኑ ጎን መቆም ይገባናል ብሏል።   "እኛ ወጣቶች ከሚለያዩን ነጠላ ትርክቶች ነፃ በመሆን ለሀገር ሰላምና ለህዝቦች አንድነት ግንባር ቀደም ተሰላፊ መሆን ይገባናል" ያለችው ደግሞ ወጣት ፅጌ ግዛው ናት። በሀገር ጉዳይ እንደማንኛውም ዜጋ ንቁ ተሳታፊ በመሆን የኮሚሽኑ ስራ ፍሬያማ እንዲሆን ወጣቶች የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባም ተናግራለች።
ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በክልሎችና ከተማ መስተዳደሮች በርካታ የቅድመ ዝግጅት እና የተሳታፊ ልየታ ስራዎችን አከናውኗል -ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ
Apr 18, 2024 484
አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 10/2016 (ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በክልሎችና ከተማ መስተዳደሮች በርካታ የቅድመ ዝግጅት እና የተሳታፊ ልየታ ስራዎች ማከናወኑን ሃገራዊ የምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ ገለጹ። ለኮሚሽኑ የሚደረጉ ድጋፎች በሃገር ግንባታ ስራዎች ላይ አሻራ የምንጥልበት በመሆኑ አስፈላጊውን የቅንጅት ስራ መስራት አንደሚገባም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ታገሰ ጫፎ ተናግረዋል፡፡ የሃገራዊ የምክክር ኮሚሽንን የአራት ወራት የሥራ የአፈፃፀም ሪፖርት የምክር ቤቱ ከፍተኛ አመራሮችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ተገምግሟል፡፡ በመድርኩ ላይ የተገኙት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤቱ አፈ -ጉባኤ አቶ ታገሰ ጫፎ እንዳሉት የምክክር ኮሚሽኑ ሃላፊነትን በተላበሰ መልኩ ተልዕኮውን ለማሳካት የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመቋቋም የህዝቦችን ዘላቂ ሰላም ለማስጠበቅ እና ለማረጋገጥ የሰራቸውን ስራዎች በጥንካሬ አንስተዋል። በሀገር ደረጃ ያሉ ችግሮችን በጋራ ለመፍታት ከችግሩ መቅድም ያስፈልጋል ያሉት አፈ -ጉባኤው ለሃገራዊ ምክክሩ ከመንግስት መዋቅርና ከፀጥታ ኃይሉ ጋር በመመካከር እንዲሁም ሌሎች ድጋፍ ሊያደርጉ የሚችሉ ተቋማት ጋር የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን በጋራ በመስራት ለሃገሪቱ ህዝብ የገባነውን ቃል መፈጸም ይኖርብናል ብለዋል። የኢትዮጵያ ሃገራዊ የምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ በበኩላቸው በክልሎችና ከተማ መስተዳደሮች በርካታ የቅድመ ዝግጅት እና የተሳታፊ ልየታ ስራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል። በዚህም በክልል ደረጃ የሚደረጉ የአጀንዳ ማሰባሰብ እና ቀሪ የምክክር ሂደቶችን አስመልክቶ የአሰራር ስርአት በመዘረጋት ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመወያየት ዋና ዋና ተግባራት መከናወናቸውን አስረድተዋል።   በቀጣይም ኮሚሽኑ የተሳታፊዎች ልየታ ባልተከናወነባቸው ክልሎች ልየታ በማድረግ አጀንዳዎችን በህዝባዊ ውይይቶች በማሰባሰብ ምክክሮች እንደሚካሄዱ ጠቁመው፤ በዚህ ሂደት የሚፈጠሩ አለመግባባቶችን ለመፍታት የሚያግዙ የሀገር ሽማግሌዎችንና በማህበሩሰቡ መካከል ተፅዕኖ ፈጣሪ የሆኑትን የመለየትና ተቀራርቦ የመወያየት ስራዎችን እንሰራለን ማለታቸውን ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተገኘው መረጃ ያመላክታል። በምክክር ሂደቱ ውጤታማ እና በሃገሪቱ የተሻለ የሰላምና የፖለቲካ መደላድል እንዲፈጠር ሁሉም የበኩሉን አስተዋፅዖ ሊያበረከት ይገባል ሲሉም ጥሪያቸውን አቅርበዋል። በመድረኩ የኢፌዴሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባዔና ምክትል አፈጉባኤን ጨምሮ የመንግስት ተጠሪዎች፣ የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢና አባላት እንዲሁም የምክር ቤቱ ከፍተኛ አመራሮች ፣ ሚኒስትሮች እና ኮሚሽነሮች፣ የመገናኛ ብዙሃን ሀላፊዎችና ሌሎችም የተለያዩ የስራ ኃላፊዎች የኮሚሽኑን የአራት ወራት የአፈፃፀም ሪፖርት አዳምጠዉ ሃሳብና አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።  
ሀገራዊ ምክክሩ የቆዩ ችግሮችን ለመፍታት ወሳኝ በመሆኑ ለስኬታማነቱ ያልተቆጠበ ትብብር እናደርጋለን--የምስራቅ ጉጂ ዞን ነዋሪዎች
Apr 18, 2024 228
ሀዋሳ ፤ ሚያዝያ 10/2016(ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ምክክሩ ለዘመናት የቆዩ ችግሮችን ለመፍታት ወሳኝ በመሆኑ ለስኬታማነቱ ያልተቆጠበ ትብብር እናደርጋለን ሲሉ በኦሮሚያ ክልል የምስራቅ ጉጂ ዞን ነዋሪዎች ገለጹ። የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በሻሸመኔ ክላስተር ከምስራቅ ጉጂ ዞን በወረዳ ደረጃ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን ወክለው በምክክር ሂደቱ ላይ የሚሳተፉ ተወካዮችን መረጣ እያካሄደ ነው።   አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የዞኑ ነዋሪዎች መካከል በሀሮ ወለቡ ወረዳ ቡርቂቱ መርመራ ቀበሌ ነዋሪው አቶ ደስታ ቡልጡ እንደገለጹት፣ በሀገራችን ለዓመታት ባልተፈቱ ቅራኔዎችና የጥላቻ ትርክት የሰላም እጦት በተደጋጋሚ ሲከሰት ይስተዋላል። በዚህም የሰው ህይወት እየተቀጠፈ፣ ንብረት እየወደመ እና ዜጎችም ከቄያቸው በመፈናቀል እንደሀገር ዋጋ እየተከፈለ መሆኑን እስታውሰዋል። ለዘመናት ያልተፈቱና ላለመግባባት እንቅፋት የሆኑ ችግሮች በቀጣይም ለህዝቦች አንድነት ፈተና ሆነው እንዳይቀጥሉ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ሥራ ዘላቂ መፍትሄ ያመጣል የሚል እምነት እንዳላቸው ተናግረዋል። በመሆኑም ለኮሚሽኑ ሥራ ስኬታማነት የበኩላቸውን እንደሚወጡ የገለጹት አቶ ደስታ፣ በተለይ የወረዳ የህብረተሰብ ተወካይነትን ዕድል ካገኙ የህብረተሰቡ የጋራ ችግሮች መፍትሄ እንዲያገኙ ጠንክረው እንደሚሰሩ ገልጸዋል።   ሌላዋ የመድረኩ ተሳታፊ ወይዘሮ ወርቅነሽ ገልቹ በበኩላቸው፣ ለልዩነት ምክንያት የሆኑ ውስብስብ ችግሮችን ፈትቶ ሀገራዊ መግባባት ለመፍጠር ምክክሩ ወሳኝ መሆኑን አመልክተዋል። "ለሀገራዊ ምክክሩ ስኬታማነት የሁላችንም ትብብር ያስፈልጋል" ያሉት ወይዘሮ ወርቅነሽ፣ አገራዊ ምክክሩ ሁሉንም የህብረተሰብ ክፍል ማሳተፉ የጋራ መፍትሄ ለማምጣት ያስችላል ብለዋል። በተለይ ለግጭት መንስኤ የሆኑ ልዩነቶችን በውይይት በመፍታት አገራዊ አንድነትን ለማምጣት ሚናው የጎላ በመሆኑ ከኮሚሽኑ ጎን ሆነው ሃላፊነታቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል። በዞኑ የዋደራ ወረዳ የሃይማኖት አባቶችን ወክለው በመድረኩ ላይ የተሳተፉት መላከሰላም ቀሲስ አለነ ቀለመወርቅ በበኩላቸው ዘመናትን የተሻገሩ ቁርሾዎች የወለዱት አለመግባባቶች በምክክርና በውይይት እንዲፈቱ መንግስት ትኩረት መስጠቱን መገንዘባቸውን ተናግረዋል። "ሁሉም ዜጋ ችግሮችን በንግግር እና በምክክር ይፈታሉ የሚል እምነት ሊኖረው ይገባል" ያሉት መላከ ሰላም ቀሲስ አለነ፣ ሀገራዊ ምክክሩ በስኬት እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን ለመወጣት ዝግጁነታቸውን አረጋግጠዋል። በኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የኦሮሚያ ተሳታፊ ልየታ ቡድን አስተባባሪ አቶ ብዙነህ አስፋ ሀገራዊ ምክክሩ በዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ መግባባትና አገራዊ አንድነት ለመፍጠር ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። በየደረጃው የሚካሄደው ምክክር ወጤት እንዲያመጣ ህዝቡ የነቃ ተሳትፎ ማድረግ እንዳለበት የገለጹት አስተባባሪው የምክክሩ ውጤታማነት በውይይቱ ተሳታፊዎች አስተዋጾ እንደሚወሰን አስገንዝበዋል። ለልዩነትና ላለመግባባት ምክንያት የሆኑ ችግሮችን በመሰረታዊነት ፈትቶ የጋራ መግባባት ለመፍጠር የሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ተወካዮች የማይተካ ሚናቸውን እንዲወጡም አሳስበዋል። በኦሮሚያ ክልል የተሳታፊ ልየታ ሥራ በአራት ክላስተሮች ተከፋፍሎ እየተካሄደ መሆኑን የገለጹት አቶ ብዙነህ፣ እስካሁን በ282 ወረዳዎች ከ5 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ተወካዮች መለየታቸውን አስታውሰዋል። ኮሚሽኑ በምስራቅ ጉጂ ዞን የህብረተሰብ ተወካዮችን ለመለየት ባዘጋጀው መድረክ ከ11 ወረዳዎች የተውጣጡ ከ1ሺህ በላይ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች በመሳተፍ ላይ ናቸው።    
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም