‎የሲዳማ ክልል ምክር ቤት መደበኛ ጉባኤ አዋጆችን እና ሹመት በማፅደቅ ተጠናቀቀ

‎ሀዋሳ ፤  ሐምሌ 9/2017(ኢዜአ) ፡-  የሲዳማ ክልል ምክር ቤት 9ኛ መደበኛ ጉባኤውን የተለያዩ አዋጆችን እና  ሹመት በማፅደቅ አጠናቀቀ ።

ምክር ቤቱ የቀረበለትን የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ሰራተኞች ረቂቅ አዋጅ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል ።

‎አዋጁ የመንግስት መስሪያ ቤቶች የተሰጣቸውን ተልዕኮ በአግባቡ እንዲወጡ፣  በሰራተኞች መካከል ፍትሀዊና አዎንታዊ ውድድር እንዲኖር ሚና ያለው እንደሆነ ተገልጿል ።


 

‎በሌላ በኩል የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት አስፈፃሚ አካላት ማቋቋሚያ ፤ ሥልጣንና ተግባር መወሰኛ  ረቂቅ አዋጅ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል ።

‎አዋጁ በሀገርና በክልል ደረጃ ያለውን ለውጥ መነሻ በማድረግ ተቋማት ለህብረተሰቡ የሚሰጡት አገልግሎቶች  ተደራሽና አካታች እንዲሆኑ ብሎም ተግባራቸውን በቅንጅት እንዲፈፅሙና ሀብትን በአግባቡ መጠቀም እንዲችሉ  ታሳቢ ያደረገ መሆኑ ተጠቅሷል ።

‎ምክር ቤቱ የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ አደረጃጀት ሥልጣን እና ተግባር ለመወሰን የወጣ ረቂቅ አዋጅንም እንዲሁ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል ።

ይህም ፖሊስ የተሰጠውን ሕገመንግስታዊ ተልዕኮውን በብቃት እንዲወጣ የሚያስችለው እንደሆነ ተጠቁሟል።

‎በተጨማሪም የሲዳማ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት የሀዋሳ ከተማ መዋቅራዊ የውስጥ አደረጃጀትን መልሶ ለማዋቀር የቀረበውን ረቂቅ አዋጅም አፅድቋል ።

‎በዚህም የሀዋሳ ከተማ በአምስት ክፍለ ከተሞችና  26 ቀበሌዎች የሚዋቀር መሆኑ ተመለክቷል።

ምክር ቤቱ የቀረቡለትን የተለያዩ ሹመቶችን አፅድቋል ።

በዚህም መሰረት ፡-

1/አቶ ቢኒያም ሰለሞንን የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የፍርድ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ፣ 

2/አቶ ገነነ ሹኔን የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የአስተዳደር ጉዳዮች ምክትል ፕሬዚዳንት ፣

3/ አቶ ፍቅረየሱስ አሸናፊን የክልሉ የመሬት አስተዳደርና ኢንቨስትመንት ቢሮ ኃላፊ 

4/ አቶ ዳዊት ዳንጊሶን የክልሉ ሠላምና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አድርጎ የሾመ ሲሆን፤  ተሿሚዎቹ  በምክር ቤቱ አባላት  ፊት ቀርበው ቃለ መሀላ ፈፅመዋል ።የምክር ቤቱ ጉባኤ መረሃ ግብሩን በዚሁ አጠናቋል። 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም