ሳይንስና ቴክኖሎጂ
የስታርታፕ ረቂቅ አዋጅ ወጣቶች ለሀገር እድገት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ መደላድል ይፈጥራል - ቋሚ ኮሚቴው
Jul 11, 2025 42
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 4/2017(ኢዜአ)፦ የስታርታፕ ረቂቅ አዋጅ ወጣቶች በስራ ዕድል ፈጠራ ያላቸውን ሚና በማሳደግ ለሀገር ኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ መደላድል እንደሚፈጥር በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ኃብት ልማት፣ ስራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ገለጸ። ቋሚ ኮሚቴው የስታርታፕ ረቂቅ አዋጅን በሚመለከት የባለድርሻ አካላት አስረጂ መድረክ አካሂዷል።   የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ ቤተልሔም ላቀው(ዶ/ር) ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ በቋሚ ኮሜቴው የተዘጋጁ ጥያቄዎችን በዝርዝር አቅርበዋል። በረቂቅ አዋጁ የተካተቱ አንቀጾች ላይ የሚስተዋሉ የግልጽነትና የትርጓሜ ለውጥ የሚያመጡ ሃሳቦች በድጋሚ ሊፈተሹ እንደሚገባ አንስተዋል። እንዲሁም የረቂቅ አዋጁን የህግ ማዕቀፍ ዝግጅት፣ የአጋር አካላት ሚና እና የአዋጁን አስፈላጊነት በሚመለከት ማብራሪያ እንዲሰጥበት ጠይቀዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ(ዶ/ር)፤ ከቋሚ ኮሚቴው ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በምላሻቸውም ረቂቅ አዋጁ እንደሀገር የሃብት ምንጭ የሆኑ አዳዲስ አማራጮችንና አሰራሮችን ለማስፋት ጉልህ አስተዋጽኦ ያበረክታል ብለዋል። በዋናነት መንግስት የወጣቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እያከናወነ ያለውን ተግባር ''ከሃሳብ እስከ አምራችነት'' የሚለውን እሳቤ የሚደግፍ መሆኑንም አንስተዋል። ረቂቅ አዋጁ የወጣቱን አምራችነት ለማሳደግ እንዲያግዝ ታልሞ በጥንቃቄ የተዘጋጀ መሆኑን ጠቁመው፥ ለዚህም አስቻይ የሆኑ የህግ ማዕቀፎችን ለማካተት ጥረት ተደርጓል ነው ያሉት። ቋሚ ኮሚቴው ረቂቅ አዋጁን በሚመለከት የሰጠው ግብረ መልስ ጉድለቶችን ለማረምና ለመፈተሽ የሚያግዝ በመሆኑ የቀጣይ የቤት ስራ በማድረግ የመፈተሽ ስራ እንደሚከናወን ገልጸዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ(ዶ/ር) በበኩላቸው፥ ረቂቅ አዋጁ ሀገሪቱ በተለያዩ ዘርፎች ያላትን የማምረት አቅም ለማጉላት እድል የሚፈጥር ነው ብለዋል። በተጨማሪም ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ ያለው አበርክቶ የጎላ መሆኑን ገልጸው፤ በእውቀትና ፈጠራ የተመሰረተ ኢኮኖሚ ለመገንባት አስቻይ ሁኔታ እንደሚፈጥር ጠቁመዋል። ረቂቅ አዋጁን ይበልጥ ለማዳበር ስታርታፖችንና ባለድርሻ አካላትን በቅርበት የማወያየትና ግብዓት የማሰባሰብ ስራ መከናወኑን ጠቁመዋል።   በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ኃብት ልማት፣ ስራ ስምሪትና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) በሰጡት ማጠቃለያ፤ የስታርታፕ ረቂቅ አዋጅ ለአካታች ኢኮኖሚ ግንባታ አስቻይ ሁኔታን እንደሚፈጥር አብራርተዋል። ረቂቅ አዋጁ ኢትዮጵያ ያላትን የወጣት ኃይል በተገቢው መልኩ ለመጠቀምና የፈጠራ ሃሳብ ጥቅም ላይ እንዲውል ለማድረግ የሚያግዝ መሆኑን ገልጸዋል። የተለያየ የፈጠራ ሃሳብ፣ ችሎታና በቴክኖሎጂ የዳበረ እውቀት ያላቸው ስታርታፖች በመረጡት መስክ ተሰማርተው ከሀገር አልፎ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ አዋጁ አዎንታዊ ሚና እንዳለው ጠቁመዋል። የስታርታፕ ረቂቅ አዋጅ ወጣቶች በስራ ዕድል ፈጠራ ያላቸውን ሚና በማሳደግ ለሀገር ኢኮኖሚ ግንባታ ጉልህ አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑንም ገልጸዋል።
በዞኑ በዲጂታላይዜሽን የታገዘ አገልግሎት ለማህበረሰቡ በመስጠት የተገልጋይን እርካታ ለማረጋገጥ ትኩረት ተደርጓል
Jul 10, 2025 89
ደብረ ብርሃን ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦በሰሜን ሸዋ ዞን በዲጂታላይዜሽን የታገዘ ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎት ለማህበረሰቡ በመስጠት የተገልጋይን እርካታ ለማረጋገጥ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን የዞኑ አስተዳደር አስታወቀ። የሰሜን ሸዋ ዞን የከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ በከተሞች የኮሪደር ልማትና በዲጂታላይዜሽን አተገባበር ላይ ዛሬ ከባለድርሻ አካላት ጋር መክሯል። የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መካሻ ዓለማየሁ በውይይቱ ላይ እንደገለጹት በከተሞች ተአማኒነት ያለው አገልግሎት ለመስጠት ዲጂታላይዜሽን የአሰራር ሥርአት እየተዘረጋ ነው።   የዲጂታል አሰራሩ በየደረጃው ያሉ የሲቪል ሰርቪስ ሠራተኞች ለተገልጋዩ ማህበረሰብ ግልጽና ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲሰጡ ከማድረግ ባለፈ ብልሹ አሰራርን ለማስወገድ ያግዛል ብለዋል። በአዲሱ በጀት ዓመት በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የተገልጋይን እርካታ ለመፍጠር ከሚሰራው ሥራ በተጨማሪ በከተሞችና በገጠር አካባቢዎች የኮሪደር ልማትን በማስጀመር የህብረተሰቡን አኗኗር ለማዘመን ትኩረት እንደሚሰጥም አስገንዝበዋል። የዞኑ ከተሞችና የገጠር አካባቢዎች ለማዘመን በሚሰራው ሥራም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን ሊወጡ እንደሚገባም አስተዳዳሪው አሳስበዋል። በዞኑ የከተማና መሰረተ ልማት መምሪያ ሃላፊ አቶ ብርቃብርቅ ተሾመ በበኩላቸው እንዳሉት ከተሞችን ለኑሮ፣ ለኢንቨስትመንትና ለቱሪዝም ምቹ ለማድረግ የኮሪደር ልማትን ጨምሮ የተለያዩ የልማት ተግባራት እየተከናወኑ ነው።   ለዚህም በዞኑ ሥር ባለችው የሸዋ ሮቢት ከተማ የኮሪደር ልማት ግንባታ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ተጀምሮ እየተከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል። በተጨማሪም ቡልጋ፣ አረርቲና ለሚ ከተሞችን ጨምሮ በዞኑ ሥር ባሉ ዘጠኝ ከተሞች የኮሪደር ልማት ስራን ለማስጀመር የሚያስችል የጥናት ሥራ ተጠናቋል ብለዋል። የአረርቲ ከተማ አስተዳደር ከተማና መሰረተ ልማት ጽህፈት ቤት ሥራ አስኪያጅ አቶ መሳይ አስታጥቄ በከተማው የኮሪደር ልማት ሥራን ለመጀመር የሚያስችል ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል።   ልማቱንና የህብረተሰቡን ተሳትፎ በማስመልከት ከከተማዋ ነዋሪዎች ጋር በስፋት ውይይት ተደርጎ የጋራ መግባባት ላይ መደረሱንም ጠቁመዋል። የእንሳሮ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አከበረኝ ዓለሙ በበኩላቸው እንደገለጹት ከሀገራዊ ለውጡ በፊት ተረስተው የቆዩ ከተሞች አሁን ላይ ትኩረት እያገኙ መሆናቸውን አስረድተዋል።   ለዚህም የለሚ ከተማ በኢንቨስትመንት እያደገች መምጣቷ አንዱ ማሳያ ነው ያሉት አቶ አከበረኝ፣ በአዲሱ በጀት ዓመት በከተማው የኮሪደር ልማትና የዲጂታላይዜሽን አሰራርን ለመጀመር ዝግጅት መደረጉን ጠቅስዋል። በውይይቱ ላይ የዞን፣ የወረዳና የከተማ አስተዳደር አመራሮች እንዲሁም ባለሙያዎችና ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።
የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም እርስ በእርስ ለመማማር እና ምርቶቻችንን ለማስተዋወቅ እድል ፈጥሮልናል- አፍሪካውያን ስራ ፈጣሪ ወጣቶች
Jul 10, 2025 79
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት የተካሄደው ሶስተኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም እርስ በእርስ ለመማማርና ምርቶቻቸውን ለማስተዋወቅ ምቹ እድል እንደፈጠረላቸው አፍሪካውያን ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ተናገሩ። ላለፉት ሶስት ቀናት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የቆየው 3ኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም ትናንት ተጠናቋል። ከፎረሙ በተጓዳኝ በተዘጋጀው ኤግዚቢሽን ላይ ምርቶቻቸውን ያቀረቡ አፍሪካውያን ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ለኢዜአ እንዳሉት ፎረሙ ትስስርን ለመፍጠርና ምርቶቻቸውን በተሻለ መንገድ መስራት የሚችሉበት ግብዓት ያገኙበት ነው። ከኡጋንዳ የመጣችው የኢማሮ ኢኖቬሽን መስራች ካይክራ ባርብራ እንዳለችው በግብርና ምርቶች ላይ እሴት በመጨመር ወደገበያ እያቀረበች ትገኛለች።   በኢትዮጵያ በተካሄደው የሶስተኛው አፍሪካ የስራ እድል ፈጠራ ፎረም መሳተፏ ትስስርን በመፍጠር የምርት ጥራትን ለማሻሻል እንደሚያስችላት ገልፃለች። ከዚምባብዌ የመጣችው የማጅስቲክ አፍሪካ ዳይሬክተር ጌትሩድ ቻምባቲ በበኩሏ በግብርና ምርት ማቀነባበር ላይ ተሰማርታ ምርቶችን ለገበያ እያቀረበች መሆኑን ተናግራለች።   የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም ከገበያ ትስስር ባለፈ እርስ በእርስ ለመማማር እድል የፈጠራና ምርቶችን ለማስተዋወቅ ያስቻላት መሆኑንም ገልፃለች። ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ይህ ለሁለተኛ ጊዜ መሆኑን የገለጹት ተሳታፊዎቹ፤ አገሪቱ በፈጣን እድገት ላይ መሆኗን መመልከታቸውንም ተናግረዋል። በኢትዮጵያ ለወጣቶች ስራ እድል ፈጠራ ምቹ የሆኑ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውን አስተውለናልም ብለዋል፡፡
በማዘጋጃ ቤቱ የተጀመረው ዘመናዊ አሰራር መጉላላትን አስቀርቶልናል - የሆሳዕና ከተማ ነዋሪዎች
Jul 10, 2025 89
ሆሳዕና፤ ሐምሌ 3/2017(ኢዜአ)፦ በሆሳዕና ከተማ ማዘጋጃ ቤት በአንድ ማዕከል አገልግሎት የተጀመረው ዘመናዊ አሰራር ሲገጥማቸው የነበረውን መጉላላት እንዳስቀረላቸው ነዋሪዎች ገለጹ። የክልሉ ከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ በበኩሉ የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን የተገልጋይ እርካታን ለማምጣት የተጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል። የሆሳዕና ከተማ ነዋሪ አቶ ሰላሙ አኒቶ ለኢዜአ እንደገለጹት፣ ከዚህ ቀደም በከተማው ማዘጋጃ ቤት ሲሰጥ የነበረው አገልግሎት ያልዘመነ በመሆኑ የተለያዩ ችግሮች ይገጥማቸው እንደነበር አስታውሰዋል። ቀደም ሲል የመረጃ አያያዙ በወረቀት ብቻ ያተኮረ በመሆኑ የፋይል መጥፋትን ጨምሮ የተለያዩ ችግሮች እየተከሰቱ ጉዳያቸውን ለማስፈጸም መጉላላት ይደርስባቸው እንደነበር ተናግረዋል። መረጃውን ለማፈላለግ በሚባክነው ጊዜና ጉልበት ነዋሪዎች ለእንግልትና ለሙስና ሲዳረጉ መቆየታቸውንም እንዲሁ። በአሁኑ ወቅት በከተማው በቴክኖሎጂ ታግዞ የተጀመረው የአንድ ማዕከል አገልግሎት ከሰው ንክኪ ውጭ መሆኑ ቀልጣፋ አገልግሎት ማግኘት ከማስቻሉ ባለፈ ይገጥማቸው የነበረን እንግልት እንዳስቀረላቸው ተናግረዋል።   ከዚህ ቀደም አገልግሎት ፈልጎ ወደ ማዘጋጃ ቤቱ የሚመጣ ነዋሪ የራሱን ማህደር እንኳ ለማግኘት መጉላላት ይገጥመው እንደነበር ያስታወሱት ሌላዋ የከተማዋ ነዋሪ ወይዘሮ ክብነሽ ሶዲሶ ናቸው። በአግባቡ የተሰደረ የመረጃ አያያዝ ስላልነበረ ጉዳይ ለማስፈጸም ለበርካታ ጊዜ በመመላለስ እንጉላላ ነበር ያሉት ነዋሪዋ፣ ለቅሬታቸው በቂ መልስ የሚሰጥ ሰው ባለመኖሩም ጉዳይን ከሙስና ውጭ ለማስጨረስ ይቸገሩ እንደነበር አስታውሰዋል። ማዘጋጃ ቤቱ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዲጂታል የታገዘ ዘመናዊ አገልግሎት መስጠት መጀመሩ ፈጣንና ተገቢ አገልግሎት ለማግኘት እንዳስቻላቸው ተናግረዋል። ጉዳያቸውን በአጭር ጊዜ መፈጸማቸውን ተናግረው፣ የመልካም አስተዳደር ችግርን በመፍታት የተጀመረው ቀልጣፋ አገልግሎት እንዲጠናከርም ጠይቀዋል።   በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የከተማና ኢንደስትሪ ክላስተር አስተባባሪና የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ቢሮ ኃላፊ ስንታየሁ ወልደሚካኤል ለኢዜአ እንደገለጹት፣ በክልሉ በማዘጋጃ ቤት ከአገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ለማረም ትኩረት ተሰጥቷል፡፡ በዚህም አገልግሎት አሰጣጡን የማዘመን ሥራ እየተሰራ መሆኑን ገልጸው፣ በዚህም የሆሳዕና ከተማን ጨምሮ በክልሉ አራት ከተሞች ሙሉ በመሉ በዲጂታል የታገዘ አገልግሎት እንዲሰጡ መደረጉንና ተስፋ ሰጪ ውጤት መታየቱን ተናግረዋል። የአገልግሎት አሰጣጡ መዘመኑ ከዚህ ቀደም በተገልጋዮች ላይ ይደርስ የነበረን እንግልትና የመልካም አስተዳደር ችግሮች መፍታት እንዳስቻለም ገልጸዋል። የማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎትን በማዘመን የተገልጋዩን እንግልት ለመቀነስ የተጀመረው ሥራ በቀጣይም በክልሉ የተለያዩ ከተሞች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አቶ ስንታየሁ አስታውቀዋል፡፡ ዘንድሮ በክልሉ በ16 ከተሞች ማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት አሰጣጥን በማዘመን ለህብረተሰቡ ፍትሀዊና ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እየተሰራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡ በተለይም መሬትና መሬት ነክ አገልግሎት፣ የግንባታ ፍቃድ እንዲሁም ከልዩ ልዩ አገልግሎት የሚሰበሰብ ክፍያና መሰል አገልግሎቶችን ዲጂታላይዝድ ለማድረግ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን ነው ያስረዱት።    
ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ዘርፍ እያከናወነች ያለው ተግባር አስደናቂ ነው -የአፍሪካ የስራ ፈጠራ ፎረም ተሳታፊ ሚኒስትሮች
Jul 9, 2025 134
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 2/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እድገቷን ለማፋጥን በቴክኖሎጂ ዘርፍ እያከናወነች ያለው ተግባር አስደናቂና ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራት ልምድ የሚወሰድበት መሆኑን በ3ኛው የአፍሪካ የስራ ፈጠራ ፎረም ተሳታፊ የሆኑ ሚኒስትሮችና የስራ ሃላፊዎች ገለጹ፡፡ የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 3ኛው የአፍሪካ የስራ ፈጠራ ፎረም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል። በመድረኩ ከተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት የተወጣጡ ሚኒስትሮች፣ ዲፕሎማቶች፣ የዘርፉ ምሁራን፣ ተመራማሪዎች፣ ሥራ ፈጣሪዎች እና የዓለም አቀፍ ድርጅቶች ተወካዮች እየተሳተፉ ይገኛሉ፡፡ ተሳታፊዎቹ ትናንት ከሰዓት በኋላ የአድዋ ድል መታሰቢያን፣ ሳይንስ ሙዚየምንና የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ተጠሪ ተቋማትን ጎብኝተዋል። በጉብኝቱ ወቅት አስተያየታቸውን ከሰጡን መካከል የጋና የሠራተኛ፣ ሥራና የሥራ ስምሪት ሚኒስትር አብዱል-ራሺድ ፔልፑዎ ፤ አዲስ አበባ በፈጣን እድገት ላይ መሆኗን መመልከታቸውን ተናግረዋል።   የመሰረተ ልማት ግንባታዎቹ የከተማዋን እድገት የሚያፋጥኑ መሆናቸውን ገልጸው፤ ኢትዮጵያ እድገቷን ለማፋጠን የጀመረቻቸው ተግባራት ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ምሳሌ ናቸው ብለዋል። የደቡብ ሱዳን የሰራተኞች ጉዳይ ሚኒስትር ጀነራል ጄምስ ሆት ማይ በበኩላቸው በሳይንስ ሙዚየም ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ዘርፍ እያከናወነች ያለውን ስራ መመልከታቸውን ነው የተናገሩት። የተመለከቷቸው ስራዎች ኢትዮጵያ ምርታማነትን ይበልጥ ለማሳደግ ዘመናዊ እርሻ ላይ ያላትን ዕቅድ የሚያሳዩ ናቸው ብለዋል።   ኢትዮጵያ የጀመረቻቸው ተግባራት በአፍሪካ ከምግብ ዋስትና ጋር ተያይዘው የሚነሱ ችግሮችን ለመቅረፍ የሚያስችሉ መሆናቸውን ገልጸዋል። ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ሀገራት ተሞክሮ የሚሆን የልማት ስራ እያከናወነች እንደምትገኝ የገለጹት ደግሞ በማላዊ የአነስተኛ እና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞችን ልማት ላይ የሚሰራ ድርጅት የቦርድ ሰብሳቢ ቦንፊስካ ዛሚራ ናቸው።   በሳይንስ ሙዚየም በተመለከቱት ስራ መደነቃቸውን የገለጹት ቦንፊስካ፤ ተግባራቱ ኢትዮጵያን በዘርፉ ከአፍሪካ ቀዳሚ ሀገር ያደርጋታል ብለዋል።    
አፍሪካ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም በአህጉሪቱ የሥራ ዕድል ፈጠራን ማስፋት አለብን - የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ
Jul 8, 2025 125
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ አፍሪካ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም በአህጉሪቷ የሥራ ዕድል ፈጠራን ለማስፋት ሀገራት በትብብር ሊሰሩ እንደሚገባ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ ሰለሞን ሶካ ገለጹ። የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 3ኛው የአፍሪካ የስራ ፈጠራ ፎረም ዛሬም ቀጥሎ ተካሂዷል። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሰለሞን ሶካ፥ የስራ አጥነት ችግር የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የአህጉሪቱ ፈተና መሆኑን አንስተዋል። የስራ አጥነት ችግርን ለማቃለል የአፍሪካ አገራት በጋራ በመስራት ከፍተኛ ውጤት ማምጣት እንደሚችሉ አንስተዋል። ስለሆነም አፍሪካ ያላትን እምቅ አቅም በመጠቀም የስራ ፈጠራን ወደ ላቀ ደረጃ ማሸጋገር ላይ ትኩረት ተደርጎ መስራት እንደሚገባ አስታውቀዋል። ለዚህም ጥሬ ዕቃ መላክ ብቻ ሳይሆን ብዙ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩ እሴት ጨማሪ የምርት ሰንሰለቶችን በመዘርጋት በዜጋ ተጠቃሚነትና በወጪ ንግድ ዕድገት ላይ ትኩረት ማድረግ የግድ ነው ብለዋል። የዲጂታል ቴክኖሎጂ፣ የፋይናንስ አካታችነት ስራዎችን በማሻሻልና የአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣናን በመተግበር ተጨማሪ የሥራ ዕድሎችን መፍጠር አስፈላጊ መሆኑንም ሚኒስትር ዴኤታው ተናግረዋል። ዜጎች ለህገወጥ ስደት እንዳይዳረጉ፣ በሀገራቸው ሰርተው እንዲለወጡና ተከብረው እንዲኖሩ አህጉራዊ ትብብር ወሳኝ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ በስራ ገበያ መረጃ ስርዓት፣ በክህሎት መር የስራ እድል ፈጠራ እና በህጋዊ የውጭ ሀገር የስራ ስምሪት ስኬታማ ተግባራትን እያከናወነች እንደምትገኝም አንስተዋል። በፎረሙ የፋይናንስ አካታችነት፣ የዲጂታልና የንግድ መሰረተ ልማቶች፣ የህግ ማዕቀፍ ክፍተቶች፣ የአፍሪካ ነጻ ንግድ ቀጣና ጉዳዮች ላይ ውይይት እንደሚደረግ ጠቁመዋል።  
ኢትዮጵያ በሥራ ዕድል ፈጠራ ከአፍሪካ ሀገራትና ከአህጉራዊ ተቋማት ጋር ትብብሯን አጠናክራ ትቀጥላለች
Jul 8, 2025 118
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በሥራ ዕድል ፈጠራ እና በክህሎት ልማት ዘርፍ ከአፍሪካ ሀገራትና ከአህጉራዊ ተቋማት ጋር ያላትን ትብብር አጠናክራ እንደምትቀጥል የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ተናገሩ። የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአጋር አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው 3ኛው የአፍሪካ የስራ ፈጠራ ፎረም ዛሬም ቀጥሎ ተካሂዷል። ከፎረሙ በተጓዳኝ የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ከአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ትሬድ ግሩፕ ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል።       የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በዚህ ወቅት እንደገለጹት ኢትዮጵያ ለወጣቶች የክህሎት ልማት እና የሥራ ዕድል ፈጠራ አበክራ እየሰራች ትገኛለች። በአህጉሪቱ የሥራ ዕድል ፈጠራን ተቋማዊ አድርጎ ከመተግበርና አሰራርን ከማመቻቸት አንጻር የአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ትሬድ ትልቅ ሚና እየተጫወተ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያም በክህሎት ልማት፣ በሥራ ገበያና መሰል ጉዳዮች ከአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ትሬድ ጋር ባለፉት ሶስት ዓመታት በጋራ ስትሰራ ቆይታለች ነው ያሉት።   በዛሬው እለት የተደረገው የመግባቢያ ስምምነትም ከድርጅቱ ጋር የሚሰሩ ስራዎችን ወደ ላቀ ደረጃ የሚያሸጋግር እና አህጉራዊ ትብብርን የሚያጠናክር መሆኑን ተናግረዋል። ድርጅቱ ኢትዮጵያ ውስጥ ቀጣናዊ ጽህፈት ቤት መክፈቱን ገልጸው፤ ይህም ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ትስስር በማሳደግ በኩል ትልቅ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል። የአፍሪካ ኤሌክትሮኒክ ትሬድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሙሉዓለም ስዩም በበኩላቸው ተቋሙ በአፍሪካ ቀጣይነት ያለው የስራ እድል ፈጠራን ለማጎልበት እየሰራ ነው ብለዋል።   ከስራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር የተደረገው ስምምነት በኢትዮጵያ የስራ እድል ፈጠራን ዘላቂነት ባለው መልኩ ለማስፋፋት የሚከናወኑ ስራዎች ላይ ድጋፍ ለማድረግ የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰዋል። በፋይናንስ ዘርፍና የገበያ ትስስር መፍጠር ስራዎች ላይ የተቀናጀ ድጋፍ በማድረግ የንግድ ድርጅቶችን አቅምና ተወዳዳሪነት ለማሳደግ ድጋፍ እንደሚያደርግም አብራርተዋል።
የቱሪዝም ዘርፉን ተወዳዳሪ ለማድረግ ፈጠራ የተሞላበት የቴክኖሎጂ ውጤቶችን መጠቀም ይገባል -የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ
Jul 8, 2025 110
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ የቱሪዝም ዘርፉን ተወዳዳሪ ለማድረግ ፈጠራ የተሞላበት የቴክኖሎጂ ውጤቶች መጠቀም እንደሚገባ የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ ገለፁ። ቱሪዝም ሚኒስቴር ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በሀገራችን የሚገኙ መዳረሻዎችን እና የቱሪዝም አገልግሎቶችን በተሻለ ሁኔታ በማስተዋወቅ “ቪዚት ኢትዮጵያ" የተሰኘ ሀገር በቀል የግብይት ድረገፅ በይፋ ስራ ጀምሯል። ቪዚት ኢትዮጵያ የቱሪዝም ዕምቅ ሀብት፣ የቱሪዝም መዳረሻዎች ለአለም የሚያስተዋውቅ ድረገፅ መሆኑ ተገልጿል።   በይፋ ማድረጊያ መርሃግብሩ ላይ የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ፣ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግሥት ሀሚድ፣ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ተስፋሁን ጎበዛይና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። የቪዚት ኢትዮጵያ የቱሪዝም መዳረሻዎችንና አገልግሎት ሰጪዎችን የሚያስተዋውቅ እንዲሁም ቻት ቦትን ያካተተ ነው ተብሏል።   በዚህ ወቅት የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ እንዳሉት ኢትዮጵያ በርካታ የቱሪዝም ፀጋዎች አሏት። የቱሪዝም ዘርፉን ተወዳዳሪ ለማድረግ ፈጠራ የተሞላበት የቴክኖሎጂ ውጤቶች መጠቀም ይገባል ብለዋል። ቪዚት ኢትዮጵያ የቱሪዝም መዳረሻዎችን የተመለከተ ወቅታዊና ጥራቱን የጠበቀ መረጃ ማቅረብ የሚያስችል መሆኑንም ተናግረዋል። የቱሪዝም ዘርፍ ተዋንያንን በአንድ በይነ መረብ የሚያስተሳስር ነው ብለዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግሥት ሀሚድ በበኩላቸው ኢትዮጵያ የበለፀገ የባህል ስብጥርና የቱሪዝም ሀብት ያላት አገር መሆኗንም ገልጸዋል።   ያለንበት የዲጂታል ዘመን ጎብኚዎች ባሉበት በመሆን ቪዚት ኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፉን አለም አቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉበት ነው ብለዋል። ቪዚት ኢትዮጵያ ደህንነቱ የተጠበቀና ተጠቃሚን ማዕከል ያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ለበርካታ ዜጎች የሥራ እድል የፈጠሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን እየተገበረች ነው
Jul 8, 2025 89
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ አዲስ አበባን ጨምሮ በሁሉም አካባቢ እያከናወነቻቸው ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ለበርካታ ዜጎች የሥራ እድል እየፈጠሩ መሆኑን መገንዘባቸውን የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም ተሳታፊዎች ገለጹ። በአዲስ አበባ እየተካሄደ በሚገኘው ሦስተኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም በአህጉሪቱ ያለውን እምቅ አቅም በመጠቀም ለአፍሪካውያን ወጣቶች የሥራ እድል ለመፍጠር ትብብርን የሚያጎለብት እንደሆነ ተሳታፊዎች ገልጸዋል። ኡጋንዳዊው ተሳታፊ ናምጎ ጆብ እንደገለጸው፤ ፎረሙ በአፍሪካ ያለውን እምቅ አቅም በመጠቀም በሥራ እድል ፈጠራ የተያዙ እቅዶችን በትብብር መተግበር ለአህጉሪቷ ወጣቶች ተስፋ የሚሰጥ ነው። ይህም አፍሪካውያን ወጣቶች በአገራቸው ሰርተው የመበልጸግ ርዕያቸውን እውን በማድረግ ከስደት እንደሚታደጋቸው ገልጿል። ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ አዲስ አበባ የመጣው እ.ኤ.አ በ2023 እንደነበር በማስታወስ፤ አሁን ለሁለተኛ ጊዜ ሲመጣ የአዲስ አበባ የመሰረተ ልማት መስፋፋትና የከተማዋ እድገት እንዳስገረመውም ጠቅሷል። የአዲስ አበባ ዘመናዊ መሰረተ ልማት፣ የከተማ ውበት፣ የጎዳናዎች ስፋትና ጽዳት "በአፍሪካ የአውሮፓ ከተማ ውስጥ እንዳለሁ ተሰምቶኛል" ሲል የከተማዋን ዕድገት አድንቋል። በከተማዋ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል የሚፈጥሩ መሆኑን መገንዘቡን በማንሳት፥ ኢትዮጵያ በብሩህ ተስፋ ጉዞ ላይ ናት ብለዋል። በኮሜሳ የሴት ነጋዴዎች ማህበር ፌዴሬሽን የቦርድ ሊቀ መንበር ሞሪን ሶቦይ ወደ ኢትዮጵያ በሚመጡበት ወቅት የሚያገኙት አዳዲስ ለውጥ ሀገሪቱ በፈጣን እድገት ላይ መሆኗን የሚያመላክት እንደሆነ ገልጸዋል።   ሌሎች የአፍሪካ አገራትም ከኢትዮጵያ የዕድገት ጉዞ ልምድ ሊወስዱ እንደሚገባ ጠቁመዋል። አዲስ አበባ በከተማ ውበት፣ እድገትና ጽዱ አካባቢን በመፍጠር እያሳየች ያለው ለውጥም ለመኖሪያ ምቹ ያደርጋታል ነው ያሉት። በኢትዮጵያ የዓለም አቀፉ የስራ ድርጅት ዋና የቴክኒክ አማካሪ አንቶኒ አይንታ ኢትዮጵያ ለራሷ ብቻ ሳይሆን ለጎረቤት አገሮችም አቅም መሆን የሚችል ብቁ የሰው ሃይል አላት ብለዋል።   አህጉሪቱን በንግድና አገልግሎት ለማስተሳሰር ከተያዘው ራዕይ ጎን ለጎን በሰለጠነ የሰው ሃይል የወጣቶችን እውቀት በመጠቀም በስራ ፈጠራ ማስተሳሰር እንደሚቻል ጨምረዋል። ሦስተኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም የግብርና እሴት ሰንሰለት፣ ዲጂታላይዜሽንና የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ አስተማማኝ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ቀጣናዊ ትስስርን ማጠናከር ላይ ምክክር በማድረግ ዛሬም ቀጥሎ ተካሂዷል።
ማዕከሉ በምርምር ያገኛቸውን አምስት የሰብልና የጥራጥሬ ዝርያዎችን ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ ለቋል
Jul 8, 2025 168
ሮቤ፤ ሐምሌ 1/2017 (ኢዜአ)፡- የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል በምርምር ያገኛቸውን አምስት የሰብልና የጥራጥሬ ዝርያዎች ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ መልቀቁን አስታወቀ። በምርምር የተገኙ ዝርያዎች አርሶ አደሩ በምግብ ራስን ለመቻል የሚያደርገውን ጥረት የሚያግዙና ተጨማሪ ገቢን በማስገኘት ረገድ የጎላ አስተዋጽኦ ያላቸው መሆኑ ተመልክቷል።   የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር አቶ ታመና ሚደቅሳ እንዳመለከቱት፤ ማዕከሉ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በምርምር እየደገፈ ነው። ማዕከሉ ባለፉት ዓመታት በምርምር ያፈለቃቸውና በሄክታር እስከ 70 ኩንታል ምርት የሚሰጡ " ቦኩ፣ ሳነቴና ሃጫሉ" የተሰኙ የስንዴ ዝርያዎችን ለተጠቃሚው ማድረሱን አውስተዋል።   በምርምር የወጡ የተሻሻሉ ዝርያዎች በማዕከሉ ማሳ ፣ በኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝና በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በስፋት ተባዝተው ለአርሶ አደሩ ተደራሽ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። አቶ ታመና ፤ ማዕከሉ ቀደም ሲል ጀምሮ ምርምር ሲያካሄድባቸው ቆይቶ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ያወጣቸው አምስት አዳዲስ የሰብልና የጥራጥሬ ዝርያዎች ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ መልቀቁን አስታውቀዋል።   በምርምር ከተለቀቁ ዝርያዎች መካከል የፓስታና ማካሮኒ ስንዴ፣ባቄላ፣ምስርና ሁለት የተልባ ዝርያዎች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል። በብሔራዊ የዝርያ አፅዳቂ ኮሚቴ ይሁንታ ካገኙ በኋላ የተለቀቁት እነዚህ ዝርያዎች በሽታን በመቋቋም ከነባሩ ዝርያዎች ከ15 በመቶ በላይ የምርታማነት ብልጫ ያላቸው መሆኑንም አክለዋል።   የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል በ1978 ዓ.ም የተቋቋመ ሲሆን፤ እስካሁን 116 የሚሆኑ የሰብልና የእንስሳት መኖ ላይ ያተኮሩ ዝርያዎችን በምርምር በማፍለቅ ለተጠቃሚው ማሰራጨቱን ከምርምር ማዕከሉ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።  
ኢትዮጵያ በአስደናቂ የለውጥ ጎዳና ላይ ትገኛለች- የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀመድ አሊ የሱፍ
Jul 7, 2025 143
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30 /2017 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በብዝሃ የኢኮኖሚ ዘርፍ በአስደናቂ የለውጥ ጎዳና ላይ ትገኛለች ሲሉ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀመድ አሊ የሱፍ ገለጹ። ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሳል አመራር በአስደናቂ የለውጥ ጎዳና ላይ እንደምትገኝም ተናግረዋል። 3ኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም መካሄድ ጀምሯል። በፎረሙ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፣ የአፍሪካ ሀገራት ሚኒስትሮች፣ የፈጠራ ባለሙያዎች፣ ሥራ ፈጣሪዎች፣ የዘርፉ ምሁራን እና ባለድርሻ አካላት ታድመዋል።   የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀመድ አሊ የሱፍ፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እንድታስመዘግብ እየሰጡ ላለው ድንቅ አመራርም አድናቆታቸውን ገልጸዋል። በአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራን እና የኢኮኖሚ ለውጥን ማሳካት የልማት ዋነኛ መሠረት ነው ብለዋል። ወጣቶችና ሴቶች የዲጂታል ክህሎት ስልጠና እና የፋይናንስ ድጋፍ እንዲያገኙ ማድረግም ይገባል ነው ያሉት። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ አስደናቂ ስኬት እያስመዘገበች መሆኗን ገልጸዋል። አዲስ አበባን ጨምሮ በርካታ የኢትዮጵያ ከተሞች በአስደናቂ እና ህይወት ቀያሪ የዕድገት ጉዞ ላይ መሆናቸውን ገልጸው፥ ይህም የድንቅ አመራር ውጤት ማሳያ ነው ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አመራር ኢትዮጵያ በግብርናው መስክም በስንዴና ሌሎች የሰብል ምርቶች ራስን ከመቻል አልፋ ኤክስፖርት እስከማድረግ ደርሳለች ነው ያሉት። ከአፍሪካ ህዝብ ከ60 በመቶ በላይ የሚሆነው ከ25 ዓመት በታች ዕድሜ ላይ የሚገኝ ወጣት ኃይል መሆኑን በማውሳት፥ በየዓመቱ የሚፈጠረው የሥራ ዕድል አሁንም አነስተኛ ነው ብለዋል። አፍሪካ በዓለም የምርት እሴት ሰንሰለት ውስጥ ያላት ድርሻም ከሦስት በመቶ በታች መሆኑን በማንሳት ይህን ከፍ ማድረግ እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል። ግብርና በአፍሪካ ከፍተኛ የሥራ ዕድል መፍጠሪያ መስክ መሆኑን ጠቅሰው፥ ከ60 በመቶ በላይ ህዝብ ህይወቱን የሚመራበትም ነው ብለዋል። የአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣናም ለሥራ ዕድል ፈጠራ ተጨማሪ አቅም እንደሆነ በማንሳት፥ ወደ ተግባር ማስገባት አለብን ብለዋል። የግሉ ዘርፍ፣ አነስተኛና ከፍተኛ ድርጅቶች በነፃ የንግድ ቀጣናው በመሳተፍ ተጠቃሚ ለመሆን እንዲዘጋጁም ጥሪ አቅርበዋል።   ቴክኖሎጂን በማስፋፋት አዳዲስ ሥራዎችን የመፍጠርን አስፈላጊነት በማንሳት፥ የወጣቶች ፈጠራን በማበረታታት ፈተናዎችን የሚቋቋም ዲጂታል ሥርዓትን እንዲገነቡ ማድረግ እንደሚገባ ጠቅሰዋል። በሁሉም መስክ አካታች ልማትን እውን በማድረግ ድህነትን ከአፍሪካ የማጥፋት ግብን ለማሳካት የጋራ ሥራ ወሳኝ መሆንም ገልጸዋል።
3ኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው
Jul 7, 2025 107
  አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30/2017(ኢዜአ)፦3ኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም በአዲስ አበባ ከተማ መካሄድ ጀምሯል። በፎረሙ ላይ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀመድ አሊ የሱፍ፣የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፣የአፍሪካ ሀገራት ሚኒስትሮች፣የፈጠራ ባለሙያዎች፣ሥራ ፈጣሪዎች እና የዘርፉ ምሁራን እና ባለድርሻ አካላት ታድመዋል። ፎረሙ አፍሪካ ያላትን እምቅ ሀብት ወደ ተጨባጭ አቅም ለመቀየር፣ የሥራ አጥነትን ትርጉም ባለው መልኩ ለመቀነስ፤ፍትሃዊ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነትንና አህጉራዊ ትስስርን ማላቅን ዓላማ አድርጎ ላለፉት ሁለት ተከታታይ ዓመታት ሲካሄድ ቆይቷል፡፡   ዘንድሮም ለሦስተኛ ጊዜ በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት ከዛሬ ጀምሮ በዓድዋ ድል መታሰቢያ በመካሄድ ላይ ሲሆን እስከ ሐምሌ 2 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ይቆያል። መድረኩ የግብርና እሴት ሰንሰለት፣ዲጂታላይዜሽንና የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ በተለይ ለሴቶችና ወጣቶች ምቹና አስተማማኝ የሥራ ዕድል ለመፍጠር የአፍሪካ አህጉራዊ ነፃ የንግድ ቀጣና ትስስርን ማላቅ ላይ ያተኮረ ምክክር ይደረግበታል። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ህብረት፣ከአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጠና ሴክሬታሪያት እና ከአፍሪካ ኤሌክትሮኒክስ ትሬድ ግሩፕ ጋር በትብብር ባዘጋጁት በዚህ ፎረም ከመላው አፍሪካ የተውጣጡ ከ1500 በላይ እንግዶች በመሳተፍ ላይ ናቸው፡፡
ብልጽግናን እውን ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ከጠባቂነት የተላቀቀ አስተሳሰብ መገንባት ቁልፍ ጉዳይ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
Jul 5, 2025 182
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 28/2017(ኢዜአ)፦ብልጽግናን እውን ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ከጠባቂነት የተላቀቀ አስተሳሰብ መገንባት ቁልፍ ጉዳይ ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስራና ክህሎት ቢሮ ከአዲስ ሚዲያ ኔትወርክ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው "የሚሰሩ እጆች ወግ" የተሰኘ ፕሮግራም በይፋ አስጀምሯል ። በመርሃ ግብሩ ላይ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ ቡዜና አልከድር፣ የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፣ የአዲስ ሚዲያ ኔትወርክ የቦርድ ሰብሳቢና የብልጽግና ፓርቲ የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሞገስ ባልቻ፣ የሃይማኖት አባቶች፡ የአገር ሽማግሌዎች፣ አባገዳዎች፣ ስራ ፈጣሪዎች፣ ወጣቶችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። ፕሮግራሙ በየ15 ቀኑ በአዲስ ሚዲያ ኔትወርክ የሚቀርብ ሲሆን በስራ ፈጠራ ረገድ ትውልድን የሚቀርጹ ሃሳቦችን የሚያንሸራሽሩበት መሆኑ ተመልክቷል። የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት ከተረጅነት በመላቀቅ ወደ ብልጽግና የሚያደርሱ ትልሞችን ይዘን እየሰራን ነው ብለዋል። የተያዘው ትልም የሚሳካው ጠንክረን ስንሰራ ብቻ ነው ያሉት ከንቲባ አዳነች ለዚህም ሰርተው የተለወጡ አገራት አብነት ሊሆኑን ይገባል ነው ያሉት። ከስራ ማማረጥና ስንፍና መላቀቅ እንደሚገባ ጠቅሰው፤ በዚህ ረገድ ማህበረሰቡ ውስጥ ግንዛቤን የማስፋቱ ጉዳይ አጽንኦት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል። በመሆኑም የሃይማኖት አባቶች፣ የአገር ሽማግሌዎች፣ አባገዳዎችን ጨምሮ ትውልድን የሚያንጹ ተቋማት የዜጎችን የስራ ባህል ለመቀየር የሚያስችሉ ግንዛቤ ፈጠራ ስራዎችን አበክረው ሊሰሩ እንደሚገባ አመልክተዋል። በትምህርት ተቋማትና በስራ ቦታዎችም ዜጎችን የማንቃት ስራ ሊጠናከር ይገባል ብለዋል። የስራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል በበኩላቸው፤ የስራ ባህልን ለማሳደግ እንደሀገር የማህበረሰብ ምርታማነት ምክክር መርሃ ግብር ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን አንስተዋል ። የምክክር መርሃ ግብሩ ማህበረሰቡ በየአካባቢው ያለውን ጸጋ በማየትና በመስራት ውጤታማ እንዲሆን በር የሚከፍት መሆኑን ጠቅሰዋል ። ፕሮግራሙ ለስራ ባህል ማደግ አስተዋጽኦ የሚያበረክት ትልቅ እርምጃ መሆኑንም ተናግረዋል።   ዘመኑ የሚጠይቀው አርበኝነት ሰርቶ በመለወጥ ራስን መቻል ነው ያሉት ሚኒስትሯ፤ የሚሰሩ እጆች ግለሰብንም አገርንም የሚያሳድጉ መንገዶች ናቸው ብለዋል ። በትኩረት ከተያዘ የስራ ባህል ላይ ተጨባጭ ውጤት እንደሚመጣ የአዲስ አበባ የኮሪደር ልማት ማሳያ መሆኑንም አንስተዋል። አገርን ለማሻገር ስራን የማሰቢያ መንገድ፤ ትጋትና ታታሪነትን መርህ በማድረግ ልንረባረብ ይገባል ሲሉም አጽንኦት ሰጥተዋል። በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ስራና ክህሎት ቢሮ ሃላፊ አቶ ጥራቱ በየነ በበኩላቸው በበጀት ዓመቱ ለ366ሺህ ስራ ፈላጊዎች ቋሚ የስራ ዕድል መፈጠሩን ተናግረዋል ። የፈጠራ ሃሳብ ያላቸው ወጣቶች ሃሳባቸውን ወደ ተግባር የሚቀይሩበት ስርአት መዘርጋቱንም ጠቁመዋል።
የግብርናውን ዘርፍ እድገት ለማስቀጠል የምርምር ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ-የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዮት
Jul 4, 2025 159
አዲስ አበባ፤ሰኔ 27/2017(ኢዜአ)፦የግብርናውን ዘርፍ እድገት ለማስቀጠል የተጀመሩ የምርምር ስራዎችን አጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዮት ገለፀ። ኢንስቲትዮቱ በቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል "በመትከል ማንሰራራት" በሚል መሪ ሃሳብ የ2017 አረንጓዴ አሻራ ማስጀመሪያ መርሃ ግብር አካሂዷል። በቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል የተለቀቁ ቴክኖሎጂዎችን የሚያሳይ ኤግዚቢሽንም ከፍቷል።   የኢትዮጵያ የግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ንጉሴ ደቻሳ (ፕ/ር) በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ ኢንስቲትዩቱ የግብርናውን ዘርፍ ለማዘመን እየሰራ ነው። የተሻሻሉ ዝርያዎችን በማውጣት የማባዛትና ለአርሶ አደሩ ተደራሽ የማድረግ፣ በአስተራረስና አመራረት ሂደት ዘዴዎች ላይ ክህሎት የማሳደግ ስራ እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። ኢንስቲትዩቱ ባሉት 23 ማዕከላት የተለያዩ የምርምር ስራዎችን በማከናወን ዘርፉን የመደገፍ ስራ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው፤በቀጣይም የግብርናውን እድገት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ የምርምር ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አብራርተዋል። በኤግዚቢሽኑ የቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከልም የተለያዩ ምርምሮችን በማካሄድ የሰብልና እንስሳት ዝርያዎችን የማባዛትና ተደራሽ የማድረግ ስራ እያከናወነ መሆኑን መመልከታቸውን ገልፀዋል። ኢንስቲትዩቱ ዛሬ በቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብርን ማስጀመሩን አንስተው፤ በ23ቱም ማዕከላት መርሃግብሩ እንደሚከናወን ጠቁመዋል። የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር ለምግብነት የሚውሉ ችግኞችን በመትከል የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የሚያስችል ነው ብለዋል።   የቢሾፍቱ ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር ዳኜ ሞጆ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ማዕከሉ ከ70 ዓመት በላይ በተለያዩ ሰብልና እንስሳት ላይ ምርምር በማድረግ ዝርያዎችን ሲያሻሽል መቆየቱን ገልጸዋል። ያከናወናቸው ተግባራት ለግብርናው ዘርፍ እድገት አስተዋፅኦ ያላቸው እንደሆኑም ተናግረዋል። በማዕከሉ በተካሄደው የአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተተከሉት የአቮካዶና ፓፓዬ የቡናና ወይራ ችግኞች መሆናቸውን ተናግረዋል። የማዕከሉ የጤና ስፖርት ማህበር ሊቀ መንበር ግዛቸው ካባ እና የሰው ሀብት ክፍል ሰራተኛ የሆኑት ወይዘሮ ድንቅነሽ አየለ፤ ዕጽዋቱ የአካባቢ ስነ ምህዳርን ለመጠበቅ የሚረዱ መሆናቸውን ጠቁመው፤ችግኞችን ከመትከል ባለፈ በመንከባከብ ለፅድቀት ለማድረስ የበኩላቸውን እንደሚወጡ አረጋግጠዋል።
የተቀናጀ የአረምና የተባይ መከላከል ዘዴን ለማስፋፋት እየተሠራ ነው-ግብርና ሚኒስቴር
Jul 4, 2025 126
አርባምንጭ ፤ሰኔ 27/2017 (ኢዜአ)፡- በሀገሪቱ የተቀናጀ የአረምና የተባይ መከላከል ዘዴን በማስፋፋት ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ እየተሠራ መሆኑን የግብርና ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ በተቀናጀ የአረምና የተባይ መከላከያ ዘዴ ዙሪያ በአርባ ምንጭ ከተማ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር እየመከረ ነው። በመድረኩ ላይ የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ መለሰ መኮንን (ዶ/ር) የግብርናው ዘርፍ ለሀገር ኢኮኖሚ ያለውን አስተዋጽኦ ለማሳደግ የተቀናጀ የአረምና የተባይ መከላከያ ዘዴን ለማስፋፋት እየሠራ ይገኛል ብለዋል። ፓርቲኒየም ወይም የቅንጨ አረም በእርሻና በግጦሽ መሬት ላይ በመስፋፋት እንዲሁም ኋይት ስኬል (Mango White scale) የተሰኘው የማንጎ በሽታ በምርትና ምርታማነት ብሎም በእንስሳትና ሰዎች ጤና ላይ አሉታዊ ጫና እያሳደረ መሆኑን ገልጸዋል።   አካባቢን ከሚበክል አሠራር በመውጣት አረምና ተባዮችን በተፈጥሯዊ ወይም ባዮሎጂካል መንገድ ለማስወገድ እየተሠራ ይገኛል ብለዋል። በተለይ ድንበር ዘለል የሆኑ አንበጣ፣ ወፎችና ሌሎች ተባዮችን ለመከላከል የአሰሳና የኬሚካል ርጭት ሥራ የሚያከናውኑ አምስት አይሮፕላኖችን ተገዝተው ወደ ሥራ መገባቱን ጠቅሰዋል። ሚኒስትር ዴኤታው ዓለም አቀፍ የስነ-ነፍሳትና ስነ-ምህዳር ምርምር ተቋም በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል በአርባ ምንጭ ዕፅዋት ማዕከል የገነባውን ስነ-ህይወታዊ ፀረ-ተባይና ፀረ-አረም ላቦራቶሪ በዛሬው ዕለት መርቀው ከፍተዋል። ዓለም አቀፍ የስነ-ነፍሳትና ስነ-ምህዳር ምርምር ተቋም ተወካይና ተመራማሪ ሚናሌ ካሴ (ዶ/ር) በበኩላቸው ተቋሙ የህብረተሰቡን የጤና፣ የሰብል፣ የስነ-ምህዳርና ሌሎች ችግሮችን በተቀናጀ መንገድ ለመፍታት ጥናትና ምርምር ሲያደርግ መቆየቱን ገልጸዋል።   ፓርቲኒየም የተሰኘውን አረም ከሌሎች ከሚወገዱ ቁሶች ጋር በማደባለቅ የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማምረት የሚያስችል ሥራ ከአርባ ምንጭ ዕፅዋት ማዕከል ጋር መስራቱን ተናግረዋል። በተጨማሪም የማንጎ በሽታን የሚከላከል ነፍሳት ማራቢያ ላቦራቶሪ ገንብተው ለዕፅዋት ማዕከሉ ማስረከባቸውን ገልጸዋል። በአርባ ምንጭ ዕፅዋት ማዕከል የተገነባው ተባይን በተባይ የመቆጣጠር ዘዴ እንዲሁም በፓርቲኒየም የተፈጥሮ ማዳበሪያ የማዘጋጀት ዘዴ ለግብርና ምርታማነት ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳለው የጠቆሙት ደግሞ የማዕከሉ ኃላፊ አቶ ሙላለም መርሻ ናቸው።   ቴክኖሎጂው ህብረተሰቡን ከኬሚካል ጥገኝነት የሚያላቅቅ ከመሆኑም በላይ የምግብ ዋስትናን የሚያረጋግጥ፣ ንጹህ አካባቢን ለትውልድ ለማስተላለፍ የሚያግዝ ነው ብለዋል። ለሁለት ቀናት በተዘጋጀው መድረክም ከኬኒያ የመጡ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ጨምሮ የፌዴራል መንግስት የሥራ ኃላፊዎች፣ ዓለም አቀፍ የስነ-ነፍሳትና ስነ-ምህዳር ምርምር ተቋም ተወካዮች፣ ተመራማሪዎች እና ማህበራት በመሳተፍ ላይ ይገኛሉ።  
የኮደርስ ስልጠና የተሻለ የዲጂታል እውቀትና ክህሎት እንድናገኝ መልካም አካጣሚ ፈጥሮልናል - ወጣቶች
Jul 4, 2025 137
ጂግጂጋ፤ ሰኔ 27/2017(ኢዜአ)፦ የኮደርስ ስልጠና የተሻለ የዲጂታል እውቀትና ክህሎት እንድናገኝ መልካም አካጣሚ ፈጥሮልናል ሲሉ በጂግጂጋ ከተማ የኮደርስ ስልጠና የወሰዱ ወጣቶች ተናገሩ። የሶማሌ ክልል የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ቢሮ በበኩሉ በክረምቱ በእረፍት ላይ የሚገኙ ወጣቶች የኮደርስ ስልጠና እንዲወስዱ ዝግጅት መደረጉን አስታውቋል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ከወሰዱ ወጣቶች መካከል ሸርማርኬ ሸኪብ አብዲ፤ የስልጠናው እድል በተለይም ለወጣቶች ጥሩ አጋጣሚ በመሆኑ ጥሩ የዲጂታል እውቀት እና ክህሎት እንድንጨብጥ እያደረገን ነው ብሏል። ከስልጠናው በቀሰመው እውቀት እና ክህሎት በመታገዝ ዌብሳይት በማበልጸግ የራሱን የንግድ ስራ ለማስተዋወቅ እየተጠቀመበት መሆኑን አንስቶ በነፃ እንዲህ አይነት የትምህርት እድል በማግኘቱ አመስግኗል። የሚገኘው እውቀት ከሀገርም ባለፈ ዓለም አቀፍ ተፈላጊ የሚያደርግ መሆኑን አንስቶ ሌሎች ወጣቶችም እድሉ እንዳያመልጣቸው መክሯል። ሌሎች ስልጠናውን ያገኙት ወጣት አብዲሸኩር መሀመድ አብዲ እና ሰከሪዬ አብዲረህማን ዓሌ፤ የኮደርስ ስልጠናው በብዙ መልኩ ጠቃሚ መሆኑን ካገኘነው እውቀትና ክህሎት ተገንዝበናል ብለዋል። የአሁኔ ዘመን የዲጂታል ቴክኖሎጂ ዘመን መሆኑን የገለጹት ወጣቶቹ መማር፣ መዘጋጀትና ከወቅቱ ጋር መጓዝ የግድ መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም በተለይም በክረምቱ መደበኛ ትምህርት ቤቶች ዝግ በመሆናቸው ወጣቶች ጊዜያቸውን የኮደርስ ስልጠና በመውሰድ እንዲጠቀሙበት አስገንዝበዋል። የክልሉ የመረጃ ማዕከል አስተዳደር ዳይሬክተር አብዲአዚዝ አብዲላሂ፤ የኢትዮ ኮደርስ ስለጠና እድሜ ሳይገድበው ለሁሉም ዜጎች በነፃ የሚሰጥ የዲጂታል እውቀት በመሆኑ ሁሉም እድሉን እንዲጠቀምበት መክረዋል። በተለይም ወጣቶች ዘመኑ የሚጠይቀውን ቴክኖሎጂ እውቅት በማዳበር ብቁና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ስልጠናው በእጅጉ የሚያስፈልጋቸው መሆኑን ተናግረዋል። በክልሉ እስካሁን ከ48ሺህ በላይ ወጣቶች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስደው ሰርተፊኬት የተሰጣቸው መሆኑን ገልጸው በክረምቱ በእረፍት ላይ የሚገኙ ወጣቶች ሁሉ የኮደርስ ስልጠና እንዲወስዱ ጥሪ አቅርበዋል።
የመጤ የአረም ዛፍ (ፕሮሶፒስ) ወደ ባዮማስ ኃይልነት በመቀየር የውጭ ምንዛሬ ወጪን ለመቀነስ እየተሰራ ነው
Jul 3, 2025 155
ድሬዳዋ፣ሰኔ 26/2017 (ኢዜአ) ፦የመጤ የአረም ዛፍን (ፕሮሶፒስ) ወደ ባዮማስ ኃይልነት በመቀየር የውጭ ምንዛሬ ወጪን ለመቀነስና የስራ ዕድል ለመፍጠር በቅንጅት እየተሰራ መሆኑን የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር አስታወቀ። የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ከፕሮሶፒስ ዛፍ የባዮማስ ኃይልን የማምረት የሙከራ ፕሮጀክት እንዲሳካ ግንባር ቀደም ተሳትፎ ላደረጉ ግለሰቦችና ተቋማት በድሬዳዋ ዕውቅናና ሽልማት አበርክቷል።   በኢትዮጵያ በጠቅላላው በ2 ሚሊዮን ሄክታር መሬት ላይ ተንሰራፍቶ የሚገኘው 'ፕሮሶፒስ' የተሰኘው መጤ አረም በአፋርና በሶማሌ ክልሎች የግጦሽና የእርሻ መሬትን በመውረር ጉዳት እያደረሰ ይገኛል።   ይህንን መጤ አረም በማጨድና በመፍጨት ለኃይል አማራጭነት በማዋል ለሲሚንቶ ፋብሪካዎች እንደ ድንጋይ ከሰል በመሆን አገልግሎት እንዲሰጥ ጥናት ሲደረግ ቆይቶ ወደ ተግባር መገባቱ ይታወቃል።   በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የአየር ንብረት ለውጥ ስራ አስኪያጅ አቶ ዳዊት አለሙ ለኢዜአ እንዳሉት፤ ኢትዮጵያ ለሲሚንቶ ምርት ኃይል አቅርቦት የድንጋይ ከሰልን ከውጭ ለማስገባት በየዓመቱ እስከ 300 ሚሊዮን ዶላር ወጪ ታደርጋለች። "ይህን ወጪ ለመቀነስ የ'ፕሮሶፒስ' ዛፍን ወደ ባዮማስ ኃይልነት ለመቀየር የተጀመረው የሙከራ ፕሮጀክት ኃይልን በማምረት ከፍተኛ አቅምን ሊፈጥር ስለሚችል ወደ ሙሉ ትግበራ እንዲሸጋገር በቅንጅት እየተሰራ ነው" ብለዋል። ለዚህ የሙከራ ስራ መሳካት ናሽናል ሲሚንቶ ያበረከተው አስተዋጽኦ በአርዓያነት የሚጠቀስ መሆኑን አንስተዋል።   ለሲሚንቶ ምርት ከውጭ የሚገባን የድንጋይ ከሰልን ምርት መጠን ለመቀነስ መጤ አረሙን ወደ ባዮማስ ኃይልነት በመቀየር የውጭ ምንዛሬን ለመቀነስ እና ለአርብቶ አደሩ የስራ ዕድል ለመፍጠር መሰራቱን አክለዋል። ሽልማቱ ከተበረከተላቸው መካከል የኢስት አፍሪካ ሆልዲንግ መስራችና ባለቤት አቶ ብዙአየሁ ታደለ በኢትዮጵያ ለሲሚንቶ ማምረቻ በውጭ ምንዛሬ የምታስገባውን የድንጋይ ከሰል ለመተካት የሚያስችል ስራ መሰራቱን ተናግረዋል። ፕሮሶፒስን ወደ ባዮማስ ኃይል ለመለወጥ ላከናወኑት የሙከራ ፕሮጀክት ዕውቅና እንደተሰጣቸው ገልፀው ወደ ባዮማስ ኃይልነት ለመለወጥም በግብፅ፣ በአውሮፓና በላቲን አሜሪካ በመዘዋወር ልምድ መቅሰማቸውን ገልጸዋል። ከኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ጋር በመቀናጀት ፕሮጀክቱን ወደ ስራ በማስገባት በናሽናል ሲሚንቶ ፋብሪካ የተደረገው የሙከራ ፕሮጀክት ስራ ውጤታማ መሆኑን ተናግረዋል። በቀጣይም የድንጋይ ከሰልን በባዮማስ በመተካት በለሚ ሲሚንቶ ፋብሪካዎች ተግባራዊ ለማድረግ መታቀዱን ጠቁመዋል። ሌሎች የሲሚንቶ ፋብሪካዎች የባዮማስ ኃይልን እንዲጠቀሙ ልምዳቸውን ለማካፈልና ለመደገፍ ዝግጁ መሆናቸውንም አስታውቀዋል።
በክረምት ወራት የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በመውሰድ የቴክኖሎጂ አቅም እና ተወዳዳሪነታችንን ለማሳደግ እንሰራለን- ተማሪዎች
Jul 3, 2025 179
ዲላ፤ ሰኔ 26/2017 (ኢዜአ)፦በክረምት ወራት ተጨማሪ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በመውሰድ የቴክኖሎጂ አቅምና ተወዳዳሪነታቸውን ለማሳደግ እንደሚሰሩ በጌዴኦ ዞን የሚገኙ ተማሪዎች ገለጹ። በዞኑ በክረምት ወራት ከ3 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለመስጠት ዝግጅት መደረጉም ተመላክቷል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ተማሪዎች መካከል የዲላ ዶንቦስኮ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ቅድስት ወርቅአየሁ ቀደም ሲል በፕሮግራም ፋንዳሜንታል ዘርፍ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስዳ የምስክር ወረቀት ማግኘቷን ገልጻለች። ይህም በሶፍት ዌር ግንባታ አቅም እንደፈጠረላት ገልጻ በክረምት ወራትም በሌሎች የኢትዮ ኮደርስ ዲጂታል ስልጠና ዘርፎች የሚሰጠውን ስልጠና በመከታተል ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግ መዘጋጀቷን ገልጻለች።   በሕጻናት ጌምና ጨዋታ በአፍሪካ ኮደረስ ቻሌንጅ ውድድር የፈጠራ ሥራዋን በማቅረብ ተሸላሚ መሆኗን ያነሳችው ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ተማሪ ከነአን አንትንብዬ ናት። ከዚህ ቀደም የወሰደችው የኮደርስ ስልጠና የፈጠራ አቅሟን እንዳሳደገላት ጠቁማ፣ በክረምት ወራት ስልጠናውን በማጠናከር ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግ መዘጋጀቷን ተናግራለች።   በዲላ ከተማ የሚገኘው ቆፌ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ቤዛኩሉ ገዛኸኝ በበኩሉ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በቀለም ትምህርት ያለውን ውስን እውቀት በማስፋት ተግባራዊ እውቀት እንዲጨብጥ ያደረገው መሆኑን ተናግሯል። ስልጠናው ለቴክኖሎጂ ያለውን ቅርበት እንዳሳደገለት ገልጾ፣ በዲጂታል ዓለም ብቁ ሆኖ ለመገኘትና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ የስልጠናው ፋይዳ የጎላ መሆኑን ተናግሯል።   የክረምት ወራት የእረፍት ጊዜውን በኢትዮ ኮደርስ ተጨማሪ ስልጠና በመውሰድ አቅሙን ለማሳደግ ማቀዱንም ገልጿል። በትምህርት ቤቱ ከ150 በላይ ተማሪዎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስደው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ የዲላ ዶንቦስኮ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህር አንዱአለም ፀጋዬ ናቸው።   ስልጠናውን የወሰዱ ተማሪዎች የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ የአስተሳሰብ አድማሳቸውን እንዲያሰፉ ከማድረግ ባለፈ ችግር ፈቺ የፈጠራ ሥራዎችን የማበልጸግ ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል። በተያዘው ክረምት ወራትም በትምህርት ቤቱ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን አጠናክሮ ለማስቀጠል ዝግጅት መደረጉን ጠቁመዋል። የጌዴኦ ዞን ሳይንስ፣ ኢንፎርሜንሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ሃላፊ አቶ ደረጀ ሾንጣ በበኩላቸው እንዳሉት በክረምት ወራት በዞኑ ከ3 ሺህ ለሚልቁ ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለመስጠት ዝግጅት ተደርጓል።   ለዚህም በከፍተኛ እና በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የስልጠና ማዕከላትን የማጠናከርና የኔትወርክ ዝርጋታ ሥራዎች መጠናቀቃቸውን ገልጸዋል። በበጀት ዓመቱ በዞኑ 9 ሺህ 714 ዜጎችን በኢትዮ ኮደርስ ለማሰልጠን ታቅዶ ወደስራ መገባቱንም አቶ ደረጀ አስታውሰዋል። እስካሁንም ስልጠናውን ለመውሰድ ከ8ሺህ በላይ ዜጎች እንደተመዘገቡ ጠቁመው፣ ከእነዚህ ውስጥ 3ሺህ 400 ዎቹ ስልጠናቸውን አጠናቀው የምስክር ወረቀት አግኝተዋል ብለዋል። በአሁኑ ወቅትም ስልጠናውን እየተከታተሉ ያሉ ዜጎች አሉ ያሉት አቶ ደረጀ፣ በክረምትም ስልጠናውን አጠናክሮ በማስቀጠል ከዕቅድ በላይ ለማስመዝገብ እንደሚሰራ ተናግረዋል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዜጎችን የቴክኖሎጂ እውቀት በማጎልበት የፈጠራ አቅማቸውንና ተወዳዳሪነታቸውን እያሳደገው መሆኑን ጠቅሰው፣ የስልጠናው ተሳታፊዎችም ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል።    
መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን እስከ መስከረም ድረስ 17 እናደርሳለን - ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር)
Jul 3, 2025 104
  አዲስ አበባ፤ ሰኔ 26/2017(ኢዜአ)፦ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን እስከ መስከረም ድረስ 17 እናደርሳለን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ሙስናን በተመለከተ ለተነሱላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። በማብራሪያቸውም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎትን እስከ መስከረም ድረስ 17 እናደርሳለን ብለዋል። ኢትዮጵያ ውስጥ መንግስታዊ ሙስና የለም ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ነገር ግን ከአገልግሎት አንጻር ትናንሽ የሙስና ተግባራት አሉ ብለዋል። ይህን ለማስተካከል ወደ ስራ የገባው መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በሶስት ወራት ብቻ 23 ተቋማትን በማካተት 124 አገልግሎቶችን እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል። አሁን አንድ ማዕከል ብቻ ነው ያለው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ እስከ መስከረም ድረስ 17 እናደርሳለን መሶብ እየተስፋፋ አገልግሎት እየዘመነ ሲሄድ የእጅ በእጅ ሙስና እየቀነሰ ይሄዳል ሲሉም አስታውቀዋል። ከዚያ ውጭ ሙስናን መፀየፍ የግለሰቦችን አመለካከትና ውሳኔን የሚጠይቅ መሆኑንም ማወቅ ይገባል ነው ያሉት። ሙስናን የምንከላከለው በስርዓት ነው፤ በዘረጋነው የመሶብ ስርዓትም ተገልጋዮች ከ90 በመቶ በላይ እርካታ አሳይተዋል ይህንን በሁሉም አካባቢዎች ማስፋት ከተቻለ ሙስና በእጅጉ ይቀንሳል ብለዋል በማብራሪያቸው።
40 የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ባለሙያዎች ዓለም አቀፍ የምስክር ወረቀት አገኙ
Jul 2, 2025 191
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 25/2017(ኢዜአ)፦ በአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ጥራት ቁጥጥርና አደጋ አስተዳደር የሰለጠኑ 40 የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ባለሙያዎች ዓለም አቀፍ የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አስታወቀ። አገልግሎቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ እንዳመለከተው፤ በኢትዮጵያ አጠቃላይ የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ስራዎችን በበላይነት ለመምራት በአዋጅ ኃላፊነት የተሰጠው ተቋሙ ከዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት (ICAO) ጋር በመተባበር በአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ ጥራት ቁጥጥርና በአቪዬሽን አደጋ አስተዳደር ዙሪያ ስልጠና የወሰዱ 40 ባለሙያዎች ዓለም አቀፍ የምስክር ወረቀት እንዲያገኙ ማድረጉን ገልጿል። የዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት ከ12 ዓመታት በኋላ በኢትዮጵያ የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አሰራሮች ላይ ባደረገው ኦዲት ሀገራችን ምንም ዓይነት የሴኪዩሪቲ ስጋት እንደሌለባት ማረጋገጡን አስታውሷል። ይህን ተከትሎም ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት የሲቪል አቪዬሽን ደኅንነት ዋና መምሪያ ጋር በተፈጠረው መልካም ግንኙነትና ትብብር ስልጠናው ከዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት በመጡ ባለሙያዎች ከሰኔ 9 እስከ ሰኔ 24 ቀን 2017 ዓ.ም በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ ተሰጥቷል። ዓለም አቀፍ የምስክር ወረቀቱ አየር መንገዱ ተደራሽ በሚሆንባቸው ሀገራት ሁሉ የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ የጥራት ቁጥጥር ተግባራትን ለማካሄድ የሚያስችል መሆኑን የገለጹት ከዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት የመጡት አሰልጣኞች፤ ባለሙያቹ ስልጠናውን በስኬት ማጠናቀቃቸውን ጠቁመዋል። ስልጣኞች ያገኙት ዕውቀት ተቋሙ ሀገራዊ ተልዕኮውን በላቀ ብቃት ለመፈፀም የሚያስችለው ከመሆኑም ባለፈ፤ ኢትዮጵያን ለአቪዬሽን ደህንነት ዘርፍ እየሰጠች ያለችው ልዩ ትኩረት ጉልህ ማሳያ ተደርጎም ሊወሰድ እንደሚችል የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት አመልክቷል። የአቪዬሽን ደህንነት ጠንካራ የጥራት ቁጥጥር ትግበራ እና የአደጋ ምላሽ አሰጣጥ ዝግጁነት የእያንዳንዱ የዓለም አቀፉ ሲቪል አቪዬሽን ድርጅት አባል ሀገራት ኃላፊነት መሆኑን ያስታወቀው አገልግሎቱ ፤ ይህም የአቪዬሽን ኢንዱስትሪውን ደኅንነት በዓለም አቀፍ ስታንዳርድ መሰረት ለማረጋገጥ እንደሚያስችል ገልጿል፡፡ በስልጠናው የተገኘውን ዕውቀት፣ ክህሎት እና የአስተሳሰብ ለውጥ በቀጣይ በአቪዬሽን ደህንነት ዘርፍ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለመሆን ለተያዘው ራዕይ እና አጠቃላይ ተቋማዊ ስትራቴጂ ግብዓት አድርጎ በማዋል የኢትዮጵያ አየር መንገድን ተመራጭነት ይበልጥ በማሳደግ ሀገራዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ ከፍተኛ ፋይዳ እንደሚኖረው አገልግሎቱ ለኢዜአ በላከው መረጃ አስታውቋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም