ሳይንስና ቴክኖሎጂ - ኢዜአ አማርኛ
ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ለዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም መሳካት መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ያደርጋል- አቶ ተመስገን ጥሩነህ
Mar 9, 2024 348
አዲስ አበባ፤ የካቲት 30/2016(ኢዜአ)፦ለዲጂታል መታወቂያ ፕሮግራም መሳካት መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና ክትትል ማድረጉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ገለጹ። ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው እንዳስታወቁት ብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም እስከ አሁን የደረሰበትን ደረጃ፣ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት፣ የወደፊት ዕቅዶችና የስራውን ሒደት በተቋሙ ተገኝተው ጎብኝተዋል። ብሔራዊ መታወቂያ በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራተጂ ውስጥ ለኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ አስቻይ ሁኔታ ተብለው ከተቀመጡ ስትራተጂዎች አንዱ መሆኑን ጠቅሰዋል። ዲጂታል መታወቂያ የዜጎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት እና አገልግሎት የማግኘት ቅልጥፍናን ለማረገጥ አይነተኛ ሚና እንደሚጫወት ገልጸዋል። የዲጂታል መታወቂያ ተጠቃሚ መሆን ለእያንዳንዱ ዜጋ አስፈላጊ በመሆኑም ለፕሮግራሙ መሳካት መንግስት ተገቢውን ድጋፍና ክትትል ማድረጉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል።
በሶማሌ ክልል 900 ቤተሰቦችን ተጠቃሚ የሚያደርግ የፀሐይ ኃይል (ሶላር) መብራት ግንባታ ፕሮጀክት ተጠናቀቀ
Mar 8, 2024 328
ጅግጅጋ፤ የካቲት 29/2016 (ኢዜአ)፦ በሶማሌ ክልል 900 ቤተሰቦችን ተጠቃሚ የሚያደርግ በፀሐይ ኃይል የሚሰራ (ሶላር) መብራት ግንባታ ፕሮጀክት ማጠናቀቁን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። በውሃና ኢነርጂ ሚኒስቴር የኢነርጂ ልማት ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ኢንጂነር ሱልጣን ወሊ የተመራ የፊዴራልና የክልሉ የመንግሥት የስራ ኃላፊዎች ቡድን ፕሮጀክቱን ጎብኝቷል። ሚኒስትር ዴኤታው በጉብኝቱ ላይ እንደገለጹት፤ በክልሉ ዋርዴር ወረዳ ኩርቱኒ ቀበሌ የሚገኘው የፀሐይ ኃይል ኤሌክትሪክ ማምረቻ ፕሮጀክት ግንባታና የሶላር ተከላ ስራ ሙሉ በመሉ ተጠናቋል። ፕሮጀክቱ 140 ኪሎ ቮልት የማመንጨት አቅም ያለው በመሆኑ ለመኖሪያ ቤቶች፣ ለማምረቻ ተቋማት፣ ለጤና፣ ለትምህርትና ለመንግስታዊ ተቋማት በቂ ኃይል ማቅረብ እንደሚችል ገልጸዋል። ከመንግሥት በተመደበ 63 ሚሊዮን ብር ወጪ የተጀመረው ፕሮጀክቱ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ውስጥ መሥመር ተዘርግቶለት አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምርም አስታውቀዋል። የኩርቱኒ ቀበሌ ነዋሪው አቶ አብዲ ኤሪኮ በሰጡት አስተያየት፤ ፕሮጀክቱ የቀበሌያቸው ነዋሪዎችን ከጨለማ እንደሚያወጣቸው ገልጸው ቀሪ ስራዎች በቶሎ ተጠናቀው አገልግሎቱ እንዲጀመሩ ጠይቀዋል ። በሚኒስትር ዴኤታው የሚመራው ቡድን ከሶማሌ ክልል በተጨማሪ በሐረሪ፣ በኦሮሚያና በሌሎች ክልሎች የፀሐይ ኃይልና የባዮጋዝ ቴክኖሎጂ ፕሮጀክቶችን የሥራ እንቅስቃሴ እንደሚጎበኝም ታውቋል።
ኢትዮ ቴሌኮም በዲጂታል አካታችነት ሴቶችን ማብቃት የሚያስችል ስምምነት “ኮኔክትድ ውሜን” ከተባለ ኢኒሼቲቭ ጋር ተፈራረመ
Mar 8, 2024 172
አዲስ አበባ፤ የካቲት 29/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮ ቴሌኮም በዲጂታል አካታችነት ሴቶችን ማብቃት የሚያስችል ስምምነት “ኮኔክትድ ውሜን” ከተባለ ኢኒሼቲቭ ጋር ተፈራርሟል። ስምምነቱ የዲጂታል ስርዓተ-ፆታ ልዩነትን ለማጥበብ እና የሴቶችን የዲጂታል ተካታችነት ማሳደግ የሚያስችል መሆኑ ተጠቁሟል። ስምምነቱን የኢቲዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ ከኢኒሼቲቩ የስራ ሃላፊዎች ጋር በስፔን ባርሴሎና መፈረማቸውን ከኢቲዮ ቴሌኮም የተገኘው መረጃ ያመላክታል። ስምምነቱ የሴቶችን የሞባይል ኢንተርኔት እና የሞባይል ገንዘብ አገልግሎት/ቴሌብር/ ተጠቃሚ ቁጥር እ.ኤ.አ እስከ 2026 በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ ያለመ ሲሆን አካታች የሞባይል ኢንተርኔት እና የዲጂታል ፋይናንስ አገልግሎቶች ማቅረብን ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡ ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ እንዳሉት ኩባንያው አሁን የሚታየውን የዲጂታል ስርዓተ-ፆታ ክፍተት ለማጥበብ የሞባይል ኢንተርኔትና የሞባይል ፋይናንሺያል አገልግሎቶችን ለሴቶች ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ ሴቶች በዲጂታል ኢኮኖሚው ንቁ ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ በቁርጠኝነት እየሰራ መሆኑ ተገልጿል።
ኦቪድ ግሩፕ የትራንስፖርት ችግርን ለመፍታት የሚያስችል የኬብል ካር ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ሊያደርግ ነው
Mar 7, 2024 282
አዲስ አበባ፤ የካቲት 28/2016(ኢዜአ)፦ ኦቪድ ግሩፕ የትራንስፖርት ችግርን ለመፍታት የሚያስችል የኬብል ካር (በገመድ ላይ ተንጠልጣይ የህዝብ ትራንስፖርት) ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ሊያደርግ መሆኑን የድርጅቱ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዮናስ ታደሰ ገለጹ። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጭነትና ለልማቱ ባላቸው ቁርጠኝነት በተለያዩ አካባቢዎች እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶች ሀገሪቷን በብዙ መልኩ ወደ ፊት የሚያራምዱ ናቸው ብለዋል። በሀገራዊ ልማትና በተለይም በግንባታው ዘርፍ እየተከናወኑ ያሉ ተግባራትን በተመለከተ ኢዜአ ከኦቪድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ዮናስ ታደሰ ጋር ቆይታ አድርጓል። ስራ አስፈጻሚው በማብራሪያቸው፣ ኦቪድ ግሩፕ በቴክኖሎጂ የታገዙ ዘመናዊ ቤቶችን ከመገንባት ባሻገር የትራንስፖርት ችግርን ለመፍታት በአዲስ አበባ የኬብል ካር ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ሊያደርግ መሆኑን ገልጸዋል። በገበታ ለሸገር፣ ገበታ ለሀገርና ገበታ ለትውልድ የኢትዮጵያን ገጽታ የሚያጎሉ የተለያዩ ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረው፣ ኦቪድ ግሩፕም በግንባታው ዘርፍ አዳዲስ ቴክኖሎጂ በመጠቀም ዘመናዊ ከተማ ለመገንባት በመንግስት የሚደረገውን ጥረት የበለጠ የሚደግፍ መሆኑን አረጋግጠዋል። ኦቪድ ግሩፕ በቴክኖሎጂ የታገዙ ዘመናዊ ቤቶችን ከመገንባት ባሻገር የትራንስፖርት ችግርን ለመፍታት በአዲስ አበባ የኬብል ካር ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ለማድረግ የፕሮጀክት ጥናት ማጠናቀቁን ይፋ አድርገዋል። የባቡር እና የመኪና መሰረተ ልማቶችን ማፍረስ ሳያስፈልግ በገመድ ላይ ተንጠልጣይ የህዝብ ትራንስፖርት ወይም ኬብል ካር ቴክኖሎጂን በአዲስ አበባ ተግባራዊ ለማድረግ ያሰችላል ብለዋል። መንግስት አቅመ ደካማና አነስተኛ ገቢ ያላቸውን ዜጎች ኑሮ ለማሻሻል የሚያደርገውን ጥረት አድንቀው ለስኬታማነቱ ኦቪድ እገዛና ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በመንግስት እየተከናወኑ ያሉ ፕሮጀክቶች የከተማዋን ገጽታ ከማሳመር ባለፈ የነዋሪዎችን ሕይወት የሚቀይሩና ተጠቃሚ የሚያደርጉ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ኦቪድ በዚህ ረገድ ከመንግስት ጋር በመተባበር የራሱን አሻራ እያሳረፈ ይገኛል ብለዋል። በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አመራር የአዋሬ መንደር ልማት እንዲሁም በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አመራር፣ በሺዎች ለሚቆጠሩ እናቶች የስራ ዕድል የፈጠረ የእንጀራ መጋገሪያ ማዕከል በመገንባት ኦቪድ መሳተፉን አንስተው ከግንባታ ባሻገር ማህበራዊ ሃላፊነቱን በተጠናከረ መልኩ ለመወጣት ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል። በሁሉም የልማት መስኮች የመንግስትና የግል ዘርፍ አጋርነት እየተጠናከረ መምጣቱን የጠቀሱት አቶ ዮናስ፤ በተለይም የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀሳብና ቁርጠኝነት ሀገሪቷን ወደ ፊት የሚያራምድ ስለመሆኑ አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሀገራዊ ዕምቅ ጸጋዎችን በማልማት ከገበታ ለሸገር እስከ ገበታ ለትውለድ ተግባራዊ ያደረጓቸው ፕሮጀክቶች ሁነኛ ማሳያ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል። የኦቪድ የቤት ግንባታ አካሄድ በተለይም አነስተኛና መካከለኛ ገቢ ያለውን ብዙሃኑን የሕብረተሰብ ክፍል በተመጣጣኝ ዋጋ፣ በአጭር ጊዜና በጥራት በመገንባት ተጠቃሚ ማድረግ መሆኑንም አስረድተዋል። በመኖሪያ ቤት ግንባታ ስራ አሁን እየተጠቀመ ካለው ቴክኖሎጂ ባለፈ በቅርቡ ሌላ ዘመናዊ የግንባታ ቴክኖሎጂ ተግባራዊ ለማድረግ መዘጋጀቱንም ገልጸዋል። በመሆኑም ኦቪድ ሀገራዊ ልማትን ከማገዝ ባለፈ በግንባታው ዘርፍ ዘመናዊ ቴክኖሎጂን የመጠቀምና በአጭር ጊዜ የማጠናቀቅ ስራውን ይቀጥላል ብለዋል።
የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ የሰው ሰራሽ አስተውሎት የሚኖረውን ሚና በውል ተረድቶ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ
Mar 5, 2024 248
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 26/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ የተጀመሩ ስራዎችን ለማጠናከር የሰው ሰራሽ አስተውሎት በውጭ ግንኙነት እና በደህንነት ላይ ያለውን ሚና በውል ተረድቶ መስራት እንደሚገባ ተገለጸ። በውጪ ጉዳይ ኢንስቲትዩት አዘጋጅነት "ዓለም አቀፋዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አስተዳደር ስርዓት ጅምሮች እና የኢትዮጵያ ትልም" በሚል መሪ ሀሳብ የፖሊሲ ምክክር መድረክ ተካሂዷል። በመድረኩ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን ዓለማየሁ፣ የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጃፋር በድሩ፣ እንዲሁም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጽህፈት ቤት ኃላፊ አምባሳደር እሸቴ ጥላሁን ተገኝተዋል። የመድረኩ ዓላማም የሰው ሰራሽ አስተውሎት በውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ ተልእኮ ላይ ያለውን ጠቀሜታ እና ተጽእኖ ማስገንዘብ መሆኑ ተገልጿል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጽህፈት ቤት ኃላፊ አምባሳደር እሸቴ ጥላሁን በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ የሰው ሰራሽ አስተውሎት በተለያዩ መስኮች የዓለምን አሰላለፍ እየቀየረ ነው። ቀደም ካሉ የቴክኖሎጂ አብዮቶች የላቀ ውጤት እንደሚያመጣ የታመነበት መሆኑን ገልጸው፥ በዚህም የአገራት የበላይነት እና ተከታይነት አይቀሬ መሆኑ እየታየ ነው ብለዋል። በዚህም ምክንያት በአገራት መካከል በጉዳዩ ላይ ድርድሮች መጀመራቸውን ገልጸዋል። አፍሪካ በዓለም መድረክ ጥቅሟን እንድታስከብር እንደ ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎትን አጀንዳ ቀደም ብለው ያነሱ አገራት የመሪነት ሚና እንዲጫወቱ እድል የሚፈጥር መሆኑንም ተናግረዋል። ከዚህ እኳያ እንደ ሀገር ሊኖር ስለሚገባው ዝግጅት እና መያዝ ስላለበት አቋም በጥናት ላይ የተመሰረተ አካሄድን መቅረጽ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅ ረገድ የሰው ሰራሽ አስተውሎት በውጭ ግንኙነት እና በደህንነት ላይ ያለውን ሚና በውል ተረድቶ መስራት እንደሚገባ ጠቁመዋል። እንዲሁም በምህዳሩ ተወዳዳሪ ሆኖ ለመገኘት ቴክኖሎጂውን መከታተል እና የተጀመሩ ስራዎችን ማጠናከር ይገባል ነው ያሉት። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጃፋር በድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ኢንስቲትዩቱ ለኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ መዳበር የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። በሰው ሰራሽ አስተውሎት የሀገሪቱ የውጪ ግንኙነትና ዲፕሎማሲ እንዲዳብር እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፥ የአስተዳደር ስርዓቱም ሀገራዊ ጥቅምን የሚያስጠብቅ እንዲሆን መስራት ያስፈልጋል ብለዋል። ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ ቴክኖሎጂን ለተለያዩ አገልግሎቶች በመጠቀም ላይ እንደምትገኝ ገልጸው ቴክኖሎጂውን በመረዳት የሚመጣውን አሉታዊ ተጽእኖ መቆጣጠር እንደሚገባ አንስተዋል። ኢትዮጵያ ዲጂታላይዜሽንን እውን ለማድረግ ስትራቴጂ ቀርጻ ተግባራዊ እያደረገች ነው ያሉት ደግሞ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን ዓለማየሁ ናቸው። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ የዲጂታል መሰረተ ልማቶችን በመገንባት ረገድ ከፍተኛ ውጤት የተመዘገበበት መሆኑን ገልጸው፥ ይህም የዲጂታል ስነ ምህዳሩ እንዲያድግ ማስቻሉን ተናግረዋል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት የዲጂታል ሽግግርን ለማሳለጥ ቁልፍ መሳሪያ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው፥ ጥቅም ላይ ሲውል በማስተዋል እና በጥንቃቄ መሆን እንዳለበት አስገንዝበዋል። ሚኒስቴሩ የሰው ሰራሽ አስተውሎት እንዲያድግ እንዲሁም ኃላፊነት የተሞላበት አጠቃቀም እንዲኖር በቁርጠኝነት እየሰራ እንደሚገኝ አመላክተዋል።
ቁልፍ ለሆኑ የመንግሥትና የሕዝብ ተቋማት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ የሳይበር ደኅንነት ጥበቃ እየተደረገ ነው
Mar 5, 2024 281
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2016(ኢዜአ)፦ ቁልፍ ለሆኑ የመንግሥትና የሕዝብ ተቋማት በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ የሳይበር ደኅንነት ጥበቃ እየተደረገ መሆኑን የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ገለጸ፡፡ የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ከኢትዮጵያ ሳይበር ደኅንነት ማኅበር ጋር ያዘጋጁት የሳይበር ደኅንነትና ዲጂታል ሽግግር ጉባዔ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው፡፡ የኢትዮጵያን የሳይበር ደኅንነትና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ ብሎም ሀገራዊ የሳይበር ሥነ-ምህዳር ለማጠናከር ኮንፍረንሱ ዓይነተኛ ሚና ይጫወታል ተብሏል፡፡ የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግስት ሃሚድ፤ ተቋሙ ቁልፍ የሆኑ የመንግሥትና የሕዝብ ተቋማትን የሳይበር ደኅንነት የማስጠበቅ ተልዕኮ በብቃት እየተወጣ ይገኛል ብለዋል፡፡ በተለይም ትላልቅና ወሳኝ የሆኑ መሠረተ-ልማቶችን፣ የፋይናንስና የሚዲያ ተቋማትን እንዲሁም ሌሎች የሳይበር ደኅንነት ጥበቃ በንቃት እየተከናወነ መሆኑን ገልፀዋል። የሳይበር ጥቃት መነሻዎች የተለያዩ ቦታዎች መሆናቸውን የገለጹት ዳይሬክተሯ፤ የመከላከሉ ሥራም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ታግዞ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የሳይበር ደኅንነትን በተመለከተ በማኅበረሰቡ ዘንድ ሰፊ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን አለማየሁ፤ የ2025 ዲጂታል ኢትዮጵያን ለማስተግበር በዘመናዊ የዲጂታል ሽግግር የሳይበር ደኅንነትን ማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን ገልፀዋል። የሳይበር ሥርዓቱን ደኅንነት ማስጠበቅ የአንድ ተቋም ኃላፊነት ብቻ አለመሆኑን ጠቅሰው፤ ተቋማትና ግለሰቦችም የበኩላቸውን ሚና ሊወጡ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሳይበር ደኅንነት ማኅበር እየሰራ ላለው በጎ ተግባር ሚኒስቴሩ የሚደግፈውና የሚያበረታታው መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ የኢትዮጵያ የሳይበር ደኅንነት ማኅበር ፕሬዝዳንት ዶክተር ብርሃኑ በየነ፤ ጉባዔው የኢትዮጵያን የሳይበር ደኅንነትና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ ብሎም ሀገራዊ የሳይበር ሥነ-ምህዳርን ለማጠናከር እንደሚረዳ ገልፀዋል፡፡ ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ጉባዔ የሳይበር ደኅንነት፣ የሳይበር ሕግ እና ተያያዥ ርዕሰ-ጉዳዮች ዙሪያ ከ12 በላይ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት እንደሚካሄድባቸውም ጠቁመዋል፡፡ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሳይበር ጥቃቶችና ተጋላጭነቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመምጣቱ በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት ከተሰነዘሩ 4ሺህ 623 የሳይበር ጥቃቶች 98 በመቶውን ማክሸፍ መቻሉ ይታወቃል። የሳይበር ጥቃቶችን ለመከላከል በተከናወኑ ተግባራት በአጠቃላይ ከ10 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር በላይ ማዳን ተችሏል።
"ዓለም አቀፋዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አስተዳደር ስርዓት ጅምሮች እና የኢትዮጵያ ትልም" ላይ ያተኮረ ምክክር እየተካሄደ ነው
Mar 5, 2024 310
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2016 (ኢዜአ)፦ ዓለም አቀፋዊ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አስተዳደር ስርዓት ጅምሮች እና የኢትዮጵያ ትልም" በሚል ርዕሰ ጉዳይ ላይ የፖሊሲ ምክክር እየተካሄደ ነው። በመድረኩ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን ዓለማየሁ፣ የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጃፋር በድሩ፣ እንዲሁም የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጽህፈት ቤት ኃላፊ አምባሳደር እሸቴ ጥላሁን ተገኝተዋል። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲቲዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ ጃፋር በድሩ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥ ኢንስቲትዩቱ ለኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ መዳበር የራሱን አስተዋጽኦ እያበረከተ ነው። በዚህም በዘርፉ ችግር ፈቺ የሆኑ ሀሳቦችን እያመነጨ መሆኑን ጠቅሰው፥ የዛሬው የውይይት መድረክም የዚሁ አካል መሆኑን ገልጸዋል። የመድረኩ ዓላማም የሰው ሰራሽ አስተውሎት በውጭ ግንኙነት እና ዲፕሎማሲ ተልእኮ ላይ ያለውን ጠቀሜታ እና ተጽእኖ ማስገንዘብ መሆኑን ገልጸዋል። የሰው ሰራሽ አስተውሎት በየጊዜው እያደገ መሆኑ ስጋትንም ይዞ መምጣቱን ጠቅሰው ከዚህ አኳያ ኢትዮጵያ በዘርፉ በንቃት መሳተፍ እንደሚገባት ጠቁመዋል።
የሳይበር ደህንነትና የዲጂታል ሽግግር ጉባኤ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀመረ
Mar 5, 2024 180
አዲስ አበባ፤ የካቲት 26/2016(ኢዜአ)፡- የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ከኢትዮጵያ ሳይበር ደህንነት ማህበር ጋር ያዘጋጁት የሳይበር ደህንነትና ዲጂታል ሽግግር ጉባኤ በአዲስ አበባ መካሄድ ጀምሯል። ጉባኤው የኢትዮጵያን የሳይበር ደህንነትና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅና ሀገራዊ የሳይበር ሥነ-ምህዳር ማጠናከር ላይ በስፋት እንደሚመከርበት ተጠቁሟል። ለሁለት ቀናት በሚካሄደው ጉባኤ የሳይበር ደህንነት፣ የሳይበር ህግ እና ተያያዥ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ ከ12 በላይ ጥናታዊ ፅሑፎች ቀርበው ውይይት እንደሚደረግባቸው ተገልጿል። ጉባኤው ማህበረሰቡ ስለ ሳይበር ደህንነት ግንዛቤ እንዲኖረው የማድረግ ዓላማ እንዳለውም ተጠቁሟል። በጉባኤው የመክፈቻ መርሃ ግብር ላይ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግሥት ሃሚድ፣ የኢትዮጵያ ሳይበር ደህንነት ማህበር ፕሬዚዳንት ዶክተር ብርሃኑ በየነን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው የዘርፉ አመራሮችና ተመራማሪዎች ተገኝተዋል።
የሳይበር ደህንነትና የዲጂታል ሽግግር ጉባኤ ነገ በአዲስ አበባ ይጀመራል
Mar 4, 2024 140
አዲስ አበባ፤ የካቲት 25/2016(ኢዜአ)፡- የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ከኢትዮጵያ ሳይበር ደህንነት ማህበር ጋር የሚያዘጋጁት ሁለተኛው የሳይበር ደህንነትና ዲጂታል ሽግግር ጉባኤ ነገ በአዲስ አበባ ይጀመራል። ሁለቱ ተቋማት በሰጡት መግለጫ፥ ለሁለት ቀናት በሚካሄደው በዚህ ጉባኤ የሳይበር ደህንነት፣ የሳይበር ህግ እና ተያያዥ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ ፅሑፎች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል ብለዋል። ጉባኤው ማህበረሰቡ ስለሳይበር ደህንነት ግንዛቤ እንዲኖረው የማድረግ ዓላማ እንዳለውም ገልጸዋል። የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ማህበረሰቡ በሳይበር ደህንነት ዙሪያ የተሻለ አረዳድ እንዲኖረው እየሰራ ስለመሆኑም ጠቁሟል።
በዓመት ለኔትወርክ ግዢ የሚወጣውን 60 ሚሊየን ዶላር ማስቀረት የሚያስችል ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ ነው
Mar 1, 2024 485
አዲስ አበባ፤ የካቲት 22/2016(ኢዜአ)፦ ሀገሪቱ በዓመት ለኔትወርክ ግዢ የምታወጣውን 60 ሚሊየን ዶላር ማስቀረት የሚያስችል ብሔራዊ የኔትዎርክ ማሳለጫ ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። ለአንድ ሳምንት ሲካሔድ የቆየው ሀገራዊ የዲጂታል አቅሞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሳምንት'ዛሬ ተጠናቋል። መርሃ ግብሩ ሀገሪቱ ያላትን የቴክኖሎጂ አቅም አሟጦ ለመጠቀምና በዘርፉ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመፍታት ያለመ ነው ተብሏል። በመርሃ ግብሩ ላይ በሚኒስቴሩ የብሔራዊ ኔትወርክ ፕሮጀክት መሪ አቶ ዳንኤል አድነው የፕሮጀክቱን አስፈላጊነት የሚዳስስ ጽሁፍ አቅርበዋል። ኢትዮጵያ እየተጠቀመች ያለው ኢንተርኔት ቨርዠን ፕሮቶኮል አለም የደረሰበት የቴክኖሎጂ ደረጃ ላይ ለመድረስ አዳጋች እንዲሆን አድርጎታል ብለዋል። በተጨማሪም በቀላሉ መልማት የሚችል የኔትወርክ ስርጭት እያለ ሀገሪቱ ለኔትወርክ ብቻ አላስፈላጊ ወጪ እንድታወጣና ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭ እንድትሆን አድርጓቷል ነው ያሉት። ተግባራዊ የሚደረገው ብሔራዊ የኔትዎርክ ማሳለጫ ፕሮጀክት ሀገሪቱን ከአላስፈላጊ ወጪና ከሳይበር ጥቃት የሚታደግ ነው ብለዋል። ፕሮጀክቱን በሙከራ ደረጃ በማልማት ተግባራዊ መደረጉን ገልጸው፤ በቀጣይ በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች ተደራሽ በማድረግ የኢንተርኔት አገልግሎቱን ፈጣንና ቀልጣፋ ለማድረግ እየተሰራ ይገኛል። ፕሮጀክቱ በሀገሪቱ እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች በቴክኖሎጂ እንዲደገፉ ለማድረግ፣ በትምህርት ስርዓቱ ላይ የተጀመረውን ቴክኖሎጂያዊ አሰራር ለማጠናከርና ተቋማት የሚሰጡትን አገልግሎቶች ለማቀላጠፍ የሚያግዝ ነው ብለዋል። ፕሮጀክቱ ሙሉ በመሉ ተግባራዊ ሲሆን በዋናነት እየተስፋፋ የመጣውን የሳይበር ጥቃት 80 በመቶ ለመቀነስ የሚያስችል መሆኑንም አክለዋል። እንዲሁም ለኢንተርኔት ግዢ ሀገሪቱ በዓመት የምታወጣውን ከ60 ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ ማዳን ያስችላል ነው ያሉት። ብሔራዊ የኔትዎርክ ማሳለጫ ፕሮጀክት የተለያዩ የሙከራ ስራዎች ተደርጎለት ስኬታማ በመሆኑ በቅርቡ ተግባራዊ እንደሚደረግም አረጋግጠዋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ይሽሩን አለማየሁ በበኩላቸው ሀገራዊ የዲጂታል አቅሞች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሳምንት በዲጂታል እና በአይሲቲ ዘርፍ የተከናወኑ ተግባራትን ለማስተዋወቅ የተካሔደ ነው። በተጨማሪም ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሒደት ውስጥ ሀገሪቱ በዘርፉ ያላትን አቅም ለማስገንዘብና ቴክኖሎጂን አሟጦ ለመጠቀም የሚያግዝ እንደነበርም ገልጸዋል። በአጠቃላይ የዲጂታል ስርዓቱን ይበልጥ ተደራሽ በማድረግ ግብይቱን ለማስፋትና ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
የከተሞች ፎረም መዘጋጀቱ ችግር ፈቺ አዳዲስ የፈጠራ ሥራዎቻችንን ለማስተዋወቅ ዕድል ፈጥሮልናል - ተሳታፊዎች
Feb 25, 2024 403
ሶዶ፤ የካቲት 17/2016(ኢዜአ)፦ በዘጠነኛው የከተሞች ፎረም ላይ መሳተፋቸው የህብረተሰቡን ችግር የሚያቃልሉ አዳዲስ የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ለማስተዋወቅ ዕድል እንደፈጠረላቸው በፎረሙ ላይ የተሳተፉ ሥራ ፈጣሪዎች ገለጹ። ከየካቲት 9 እስከ 15/2016 በወላይታ ሶዶ በተካሄደው 9ኛው የከተሞች ፎረም ላይ የተሳተፉ ሥራ ፈጣሪዎች እንደገለጹት በፎረሙ የተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች መሳተፋቸው አብሮነትን ለማጠናከር የሚያስችል ነው። የህብረተሰቡን ችግር የሚያቃልሉ አዳዲስ የፈጠራ ሥራዎቻቸውን ለማስተዋወቅ ፎረሙ የተሻለ ዕድል እንደፈጠረላቸውም ለኢዜአ ገልጸዋል። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ሥራ ፈጣሪዎች መካከል የወራቤ ከተማ ነዋሪው አቶ ረሻድ ከድር በእናቶች እና አርሶ አደሮች ላይ የሚስተዋለውን የሥራ ጫና ማቃለል የሚያስችል የእንሰትና የቆጮ መፋቂያ፣ የጤፍ መውቂያ እንዲሁም የቃጫ ማምረቻ ማሽኖች ማቅረባቸውን ጠቅሰዋል። ይህም የፈጠራ ሥራዎቻችንን ለማስተዋወቅ የተሻለ እድል ፈጥሮልናል ሲሉም ገልጸዋል። በወላይታ ዞን የአረካ ከተማ ነዋሪውና በአውደ ርዕዩ ላይ የሰራውን መኪና ይዞ የቀረበው ወጣት አጃዬ ማጆር በበኩሉ ፎረሙ ያለንን የፈጠራ ውጤት ለሌሎች ለማስተዋወቅ ረድቶናል ብሏል። የባለ ሁለት እግር ሞተር ሳይክል ሞተርን በመጠቀም መኪናውን እንደሰራ የተናገረው ወጣቱ፣ የፈጠራ ሥራዎች እየተጠናከረ መምጣት የውጭ ምንዛሬን ከማስቀረት ባለፈ ለዜጎች የሥራ ዕድል ለመፍጠር እነደሚያስችልም አክሏል። በ8ኛው የከተሞች ፎረም ላይ በፈጠራ የተሰሩ መኪኖች ለእይታ እንዳልቀረቡ ያስታወሰው ወጣት አጃዬ፣ ዘንድሮ ለ9ኛ ጊዜ በተካሄደው የከተሞች ፎረም ላይ የተለያዩ መኪኖች ቀርበው መመልከቱን ተናግሯል። የፈጠራ ሥራዎች እያደጉ መምጣት ሥራ ፈጣሪዎችን በማነቃቃት ሀገራዊ አድገትን ለማፋጠን የራሱ ጠቀሜታ እንዳለውም ጠቁሟል። ፎረሙ ከተሞች ያላቸውን ሀብትና የሥራ ፈጠራ ውጤት እንዲያስተዋውቁ እድል መፍጠሩን የተናገሩት ደግሞ የአርባ ምንጭ ከተማ ነዋሪው አቶ ዳዊት አብርሃም ናቸው። በአካባቢው በስፋት የሚመረተውን የሙዝ ምርት ወደ ዱቄት፣ ገንፎ፣ ኬክና ሌሎች ጣፋጭ ምግቦች እንዲሁም ኮባውን ወደ ቃጫነት ቀይሮ የሚሰራ ማሽን ሰርተው ፎረሙ ላይ ለእይታ ማቅረባቸውን ጠቅሰዋል። ከዚህ በፊት ከእንሰት ውጤት ይገኝ የነበረውን ቃጫ በአሁኑ ወቅት ከሙዝ እያመረቱ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ዳዊት፣ ፎረሙ ይሄንና አዳዲስ ፈጠራዎችን ከማቅረብ ባለፈ ሥራ ፈጣሪዎችን እርስ በእርስ ያስተዋወቀ መሆኑን ተናግረዋል። የከተሞች ፎረም "የዘመኑ ከተሞች ለኢትዮጵያ ብልጽግና" በሚል መሪ ሀሳብ ከየካቲት 9 እስከ 15 ቀን 2016 ዓ.ም በርካታ ከተሞች በተሳተፉበት በወላይታ ሶዶ ከተማ መካሄዱ የሚታወስ ነው።
አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ለሲዳማ ክልል የደህንነት ካሜራዎች ድጋፍ አደረገ
Feb 24, 2024 436
አዲስ አበባ፤ የካቲት 16/2016(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ለሲዳማ ክልል የፀጥታ ተቋማትን ለማጠናከር የሚያገለግሉ የደህንነት ካሜራዎች ድጋፍ አደረገ፡፡ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ቴክኖሎጂ አቅምን የተላበሱት የደህንነት ካሜራዎቹ ግምታዊ ዋጋቸው 25 ሚሊዮን ብር መሆኑን የኢንስቲትዩቱ መረጃ ያመለክታል። ካሜራዎቹ የሐዋሳ ከተማን እንዲሁም የክልሉን ፖሊስ አሰራር በዘመናዊ ቴክኖሎጂ በማዘመን የዜጎችን ደህንነት ለማስጠበቅ ጉልህ ሚና እንደሚኖራቸው በርክክቡ ወቅት ተጠቅሷል፡፡ የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ይታገሱ ደሳለኝ ለሲዳማ ክልል የሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ አለማየሁ ጢሞቲዎስ ካሜራዎቹን እና ተያያዥ የቴክኖሎጂ ቁሳቁሶችን አስረክበዋል። በርክክቡ ወቅትም አቶ አለማየሁ ጢሞቲዎስ ባስተላለፉት መልዕክት ኢንስቲትዩቱ ለክልሉ መንግሥት ላደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ የተረከቧቸው ቴክኖሎጂዎች ክልሉን ለማዘመን በሚደረገው ጥረት ላይ የሚኖራቸው ሚና ጉልህ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
የመጀመሪያው የዲጂታል ኢትዮጵያ ሳምንት ከየካቲት 18 እስከ የካቲት 22 ይካሄዳል
Feb 24, 2024 471
አዲስ አበባ፤ የካቲት 16/2016(ኢዜአ)፦የመጀመሪያው የዲጂታል ኢትዮጵያ ሳምንት ከየካቲት 18 እስከ የካቲት 22 እንደሚካሄድ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ ለመገናኛ ብዙሀን በሰጠው መግለጫ የመጀመሪያው የዲጂታል ኢትዮጵያ ሳምንት "የጋራ ጥረታችን ለዲጂታል ኢትዮጵያችን" በሚል መሪ ሀሳብ በሃገር አቀፍ ደረጃ እንደሚካሄድ አስታውቋል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሹሩን አለማየሁ (ዶ/ር) በአስር ዓመት የልማት ዕቅድ ውስጥ ቴክኖሎጂ ቁልፍ ሚና እንዲጫወት ለማስቻል እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። በመሆኑም የዲጂታል ኢትዮጵያ ሳምንት በዲጂታል ቴክኖሎጂ ላይ ንቅናቄ በመፍጠር የህብረተሰቡን ቴክኖሎጂ የመጠቀም ባህል በማሳደግ በልማትና ምጣኔ ሀብት ላይ ያለውን አስተዋጽኦ ከፍ ለማድረግ ያለመ እንደሆነ ተናግረዋል። በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አዘጋጅነት የሚካሄደው ይህ የዲጂታል ሳምንት ለማህበረሰቡ የኢትዮጵያን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ስራዎች ለማስተዋወቅ፤ የዲጂታል ቴክኖሎጂዎችን እንዲጠቀም ግንዛቤን ለመፍጠር ያለመ ነው ተብሏል። ሳምንቱ መንግስት የዲጂታል ቴክኖሎጂን ለልማትና ምጣኔ ሀብት ዕድገት በማዋል የማህበረሰቡን የዕለት ከእለት እንቅስቃሴ ቀላል እና ቀልጣፋ ለማድረግ እያከናወናቸው ያሉ ዘርፈ-ብዙ ተግባራትን የሚያሳይበት እንደሆነ ተገልጿል። በዲጂታል ኢትዮጵያ ሳምንት የፓናል ውይይቶች፣ ጉብኝቶችና ሌሎች በዘርፋ ግንዛቤ የሚፈጥሩ ሁነቶች የሚከናወኑ ሲሆን የዘርፉ የክልል ሀላፊዎችና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች እንደሚሳተፉ ተነግሯል።
የዲጂታል የአድራሻ ሥርዓትን በ73 ትላልቅና መካከለኛ ከተሞች ተግባራዊ ለማድረግ እየተሰራ ነው
Feb 22, 2024 373
አዲስ አበባ፤ የካቲት 14/2016(ኢዜአ)፦ የዲጂታል የአድራሻ ሥርዓትን በ73 ትላልቅና መካከለኛ ከተሞች ተግባራዊ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር በለጠ ሞላ ገለፁ። በኢትዮጵያ የስፔስ ሳይንስና ጂኦ-ስፓሻል ኢንስቲትዩት የለማው የቢሾፍቱ ከተማ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት ተግባራዊ ሆኗል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር በለጠ ሞላ በዚሁ ጊዜ እንደገለፁት፤ ሚኒስቴሩ አገሪቱን ወደ ሁለንተናዊ ብልፅግና ለማሸጋገር የሚያስችሉ የተለያዩ የቴክኖሎጂና የምርምር ሥራዎችን በማከናወን ላይ መሆናቸውን ገልፀዋል። በዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ውስጥ የዲጂታል መሠረተ-ልማትና ትስስር ትኩረት የተሰጣቸው ጉዳዮች እንደሆኑ ገልፀው፤ የዲጂታል መታወቂያና የኤሌክትሮኒክስ አገልግሎቶችም ተጠቃሽ መሆናቸውንም እንዲሁ። ሌላው የዲጂታል ኢኮኖሚ እውን እንዲሆን ቁልፍ የአስቻይነት ሚና ከሚጫወቱት ውስጥ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት በቀዳሚነት የሚጠቀስ እንደሆነ ጠቅሰው፤ ሥርዓቱ በ73 ትላልቅና መካከለኛ ከተሞች ተግባራዊ ለማድረግ ታቅዶ እየተሰራ ነው ብለዋል። በዛሬው ዕለት የተመረቀው የቢሾፍቱ ከተማ ዲጂታል የአድራሻ ሥርዓትም የዚህ ዕቅድ አካል መሆኑን ገልጸው፤ ዲጂታል የአድራሻ ሥርዓት በአገር አቀፍ ደረጃ ሙሉ በሙሉ ሲተገበር ለእያንዳንዱ ቤትና ሕንፃ እንዲሁም መንገዶች ዲጂታል አድራሻ እንዲኖራቸው የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰዋል። ይህም ብቻ ሳይሆን ለሌሎች ዲጂታል መሠረተ-ልማቶች አስቻይ ሁኔታ ይፈጥራል ነው ያሉት። በኢትዮጵያ የስፔስ ሳይንስና ጂኦ-ስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ በበኩላቸው፤ ዛሬ የተጀመረው የቢሾፍቱ ከተማ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት ኢንስትቲዩቱ ትኩረት ሰጥቶ ከሚያከናውናቸዉ ለውጥ አምጪ ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ ነው ብለዋል። ኢንስቲትዩቱ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት በአዳማና በአዲስ አበባ ከተማ ገቢራዊ ለማድረግ ከሁለቱ ከተማ መስተዳድሮች ጋር ሥምምነት በመፈጸም ወደ ሥራ መግባቱን ተናግረዋል። የአዳማ ከተማ ሥራው 70 በመቶ መድረሱን ገልፀው፤ የአዲስ አበባ ከተማም አስተዳደሩ ሥራውን በይፋ መጀመሩን ጠቁመዋል። በቀጣይም ሥራውን ወደ ሌሎች የክልል ከተሞች በማስፋት ሁሉንም ትላልቅና መካከለኛ ከተሞችን ለማዳረስ እየተሰራ ነው ብለዋል። የቢሾፍቱ ከተማ ከንቲባ አለማየሁ አሰፋ በበኩላቸው፤ ሥርዓቱ አገልግሎት ሰጪ ተቋማትና የተገልጋዮችን መስተጋብር ምቹ የሚያደርግ ነው ብለዋል። ከተማ አስተዳደሩ በዲጂታል የጀመራቸውን አገልግሎቶች ለማቀላጠፍ እንደሚያስችል ገልፀው፤ ሥርዓቱ ተግባራዊ እንዲሆን ድጋፍ ላደረጉ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።
የአፍሪካ ሀገራት የዲጂታል መታወቂያ ሥርዓትን ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ በትኩረት መሥራት አለባቸው
Feb 22, 2024 223
አዲስ አበባ፤ የካቲት 14/2016 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሀገራት የዲጂታል መታወቂያ ሥርዓትን ሙሉ ለሙሉ ተግባራዊ በማድረግ ዘላቂ ምጣኔ ኃብታዊ እድገት ለማስመዝገብ መሥራት እንዳለባቸው ተመላከተ። 12ኛው በስታትስቲክስ ላይ ያተኮረ ውይይት በበይነ-መረብ በመታገዝ መካሄዱን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን(ኢሲኤ) ለኢዜአ በላከው መግለጫ አመላክቷል። በኢሲኤ የቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ዋና ኃላፊ ማክታር ሴክ የዲጂታል መታወቂያ የምጣኔ ኃብት እድገት ላይ እሴት እንደሚጨምር ገልጸዋል። በተለይም የምጣኔ ኃብት ፍሰትን ሕጋዊ በማድረግ፣ አካታች የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት ማበረታታትና የዲጂታል የመረጃ ልውውጥ እንዲጨምር በማድረግ የሚኖረውን ሚናም ዘርዝረዋል። ሀገራት የዲጂታል መታወቂያን ተግባራዊ በማድረግ እ.አ.አ በ2030፤ ከ3 እስከ 13 በመቶ ዓመታዊ የሀገር አጠቃላይ ምርታቸው ላይ እንደሚጨምሩ በዘርፉ የተሰሩ ጥናቶች እንደሚያመላክቱ ተናግረዋል። የምጣኔ ሃብት እሴትን በመጨመር ብቻ ሳይሆን የትምህርት፣ ጤና የሥራ ገበያና ሌሎች አገልግሎቶችን በማበረታታትና አካታችነታቸው እንዲጨምር በማድረግ ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አንስተዋል። ውጤታማ የዲጂታል መታወቂያ ሥርዓት ትግበራን እውን ለማድረግ እንደየሀገራዊ ነባራዊ ሁኔታው ችግሮችን ለይቶ መፍታትና በዘርፉ ቅንጅታዊ አሰራሮች መጠናከር እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። በኢሲኤ የአፍሪካ ስታቲስቲክስ ማዕከል ዳይሬክተር ኦሊቨር ቺንጋንያ በበኩላቸው የዲጂታል መታወቂያ ሥርዓት ሁሉም ዜጎች በፍትኃዊነት በመንግሥት መስተናገዳቸውን የሚያረጋግጥ መሆኑን ተናግረዋል። በአፍሪካ 542 ሚሊየን ዜጎች የመለያ ካርድ እንዳሌላቸው ያመላከቱት ደግሞ በኢሲኤ የሥነ-ሕዝብና ማኅበራዊ ስታትስቲክስ ዋና ኃላፊ ዊሊያም ሙህዋቫ ናቸው። ከእነዚህ መካከል እድሚያቸው ከአምስት ዓመት በታች የሆኑ 95 ሚሊየን ሕጻናት የልደት ምዝገባ ያላደረጉ ሲሆን 120 ሚሊየን ደግሞ የልደት ካርድ የላቸውም ብለዋል። ሀገራት ሁሉም ሰው ሕጋዊ የመሆን መብቱን ለማረጋገጥ የፖለቲካ ቁርጠኝነት፣ የተቋማት ግንባታና ግንዛቤ መፍጠር ላይ መሥራት እንዳለባቸውም ጠቁመዋል። ኢትዮጵያ የዲጂታል መታወቂያ ሥርዓትን በመዘርጋት ነዋሪዎች የመታወቅ መብታቸው እንዲረጋገጥና ሌሎች መብቶችን የመጠቀም እድሎችን ለማስፋት የዲጂታል መታወቂያ አዋጅን ከ2015 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ እያደረገች ትገኛለች።
በቢሾፍቱ ከተማ የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት ተግባራዊ ሆነ
Feb 22, 2024 262
አዲስ አበባ፤ የካቲት 14/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የስፔስ ሳይንስና ጂኦ-ስፓሻል ኢንስቲትዩት የለማው የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት በቢሾፍቱ ዛሬ ተመርቆ ወደ ሥራ ገባ። በማስጀመሪያው መርኃ-ግብር የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶክተር በለጠ ሞላ ጨምሮ የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ፣ የቢሾፍቱ ከተማ ከንቲባ አቶ አለማየሁ አሰፋ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል። ዛሬ ተመርቆ የተጀመረው የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት በከተማዋ የሚገኙ የተቋማትና መኖሪያ ቤቶችን ትክክለኛ መገኛ ሥፍራ ለማመላከት እንደሚረዳም ተጠቁሟል። የመሬት አስተዳደርና ሌሎች የከተማዋን መረጃዎችን ለማዘመን እንደሚያስችልና አገልግሎት ሰጭ ተቋማትና የተገልጋዮችን መስተጋብር ምቹ የሚያደርግ እንደሆነም ተመላክቷል። ዲጂታል የአድራሻ ሥርዓት ማንኛውንም አስተዳደራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ አገልግሎቶችን ቀልጣፋ በሆነ መንገድ ለሁሉም ተደራሽ ለማድረግ የሚያስችል ነው ተብሏል። ቴክኖሎጂው ለነዋሪዎች ምቹ የሆኑ ከተሞችን ለመገንባት፣ ለጀማሪ የቴክኖሎጂ ሥራ ፈጣሪዎች ልዩ ልዩ የሥራ ዕድሎችን የሚፈጥርና የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን የሚያሳድግ ነው ተብሏል። በተጨማሪም የነዋሪዎችን ከቦታ ቦታ የሚደረግ እንቅስቃሴ ለማቃለል፣ቀልጣፋ ለማድረግና የኤሌክትሮኒክስ ግብይትን እውን ለማድረግ ጉልህ አስተዋጽዖ እንደሚያበረክት ተጠቁሟል። የዲጂታል አድራሻ ሥርዓት የከተሞች የአገልግሎት አሰጣጥን ማቀላጠፍን ጨምሮ የማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴን ለማዘመን እንደሚረዳም ተገልጿል። የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታውን በሚፈለገው ጥራትና ፍጥነት ተግባራዊ ለማድረግም የሚያስችል መሆኑንም እንዲሁ። በአጠቃላይ የዜጎችን ሁለንተናዊ ደኅንነት በመጠበቅ ለአንድ አገር ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ እድገት ያለው አስተዋጽኦ የጎላ እንደሆነ ተገልጿል።
ኢትዮ ቴሌኮም ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሂደት ውስጥ የመሪነቱን ሚና እየተወጣ ይገኛል
Feb 20, 2024 343
አዲስ አበባ፤ የካቲት 12/2016(ኢዜአ)፦ኢትዮ ቴሌኮም ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሂደት ውስጥ የመሪነቱን ሚና እየተወጣ እንደሚገኝ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ። ኢትዮ ቴሌኮም በኢትዮጵያ ሁለንተናዊ የዕድገት ግስጋሴ ውስጥ ከፍተኛ ሚና ከሚጫወቱ የመንግስት የልማት ድርጅቶች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል። ኩባንያው ከመደበኛ አገልግሎቱ ባሻገር የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ እና የዲጂታል አገልግሎቶችን በስፋት ተደራሽ በማድረግ የዲጂታል ኢትዮጵያን ራዕይ ለማሳካት በርካታ ሥራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛል። ይህን ተከትሎ ኩባንያው ባለፉት የለውጥ ዓመታት የኢንተርኔት ተጠቃሚ ደንበኞቹን ቁጥር በ 104 በመቶ ማሳደግ መቻሉ ተገልጿል። ከ ኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የኩባንያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ እንዳሉት ኩባንያው ዜጎች ቴክኖሎጂን ተጠቅመው የእለት ተእለት እንቅስቃሴያቸውን እንዲያቀላጥፉ የሚረዱ ምቹ ሁኔታዎችን እየፈጠረ ይገኛል። እንዲሁም ተቋማት ውጤታማ እንዲሆኑ፣ አገልግሎታቸውን በፍጥነት ተደራሽ እንዲያደርጉና ምርታማነታቸው እንዲጨምር የሚረዱ ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ባለፈ ቴክኖሎጂን መሰረት ያደረጉ አዳዲስ የስራ እድሎችን ለመፍጠር የሚያስችሉ በርካታ ትሩፋቶችን ማበርከቱን ተናግረዋል። ከለውጡ በፊት የነበሩት የኩባንያው ደንበኞች 37 ሚሊዮን እንደነበሩ በማስታወስ በ 2016 አጋማሽ ይህ ቁጥር 74 ነጥብ 6 ሚሊዮን መድረሱን ጠቁመዋል። ውጤቱ የተገኘው ሪፎርሙን ተከትሎ በተከናወኑ ስራዎች እና በየጊዜው በሚደረጉ ማሻሻያዎች መሆኑን ገልጸው ምጣኔው የ97 በመቶ ዕድገት የታየበት መሆኑን አንስተዋል። ከዚህ ቀደም የነበረው የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ቁጥር 17 ነጥብ 8 ሚሊዮን እንደነበር ገልጸው አሁን ላይ ይህ ቁጥር 36 ነጥብ 4 ሚሊዮን መድረሱን ተናግረዋል። መንግስት ለዜጎች የሚሰጠውን አጠቃላይ አገልግሎት ዲጂታላይዝ ለማድረግ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ኢትዮ ቴሌኮም አስቻይ ሁኔታዎችን የመፍጠር ስራዎቹን በጥራት እየተወጣ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ቀደም ሲል 20 በመቶ የነበረው የስማርት ስልክ ተደራሽነት አሁን ላይ ወደ 46 በመቶ ማደጉን ጠቁመዋል። ለዕድገቱ መሰረት የሆነውን ቴክኖሎጂ በማዳረስ ረገድ አሁን ላይ 340 የሚሆኑ ከተሞች የ 4ጂ አገልግሎት እንዲያገኙ መደረጉን ተናግረዋል። የብሮድባንድ አገልግሎት ከአንድ ሀገር ዕድገት ጋር ቀጥታ ግንኙነት እንዳለው ገልጸው አሁን ላይ የተጠቃሚ ደንበኞች ቁጥር 688 ሺህ መድረሱን ገልጸዋል። በዚህም በርካታ ተቋማት ያለምንም የቴክኖሎጂ ውስንነት በሀገር ውስጥ እና በውጭ ስራቸውን መከወን የሚችሉበት ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ተናግረዋል። ኩባንያው ዲጂታል ኢትዮጵያን እውን በማድረግ ሂደት ውስጥ የመሪነቱን ሚና እየተወጣ እንደሚገኝ ዋና ስራ አስፈጻሚዋ አስታውቀዋል።
በኢትዮጵያ፣ ቻይና እና ዩኤንአይዲኦ መካከል የሶስትዮሽ የትብብር ስምምነት ተፈረመ
Feb 19, 2024 232
አዲስ አበባ፣ የካቲት 11/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የልህቀት ማዕከላት ማቋቋሚያ የሦስትዮሽ ትብብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት በኢትዮጵያ፣ በቻይና እና ዩኤንአይዲኦ መካከል ተፈርሟል። የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት በኢትዮጵያ የልህቀት ማዕከላት ማቋቋሚያ የሦስትዮሽ ትብብር የጋራ መግለጫ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት በኢትዮጵያ መንግስት፣ በቻይና መንግስት እና ዩኤንአይዲኦ መካከል መፈረሙን በማህበራዊ ትስስር ገጹ ባሰፈረው መረጃ አስታውቋል። በፈጠራ የታገዙ መፍትሄዎችን ለማስገኘት በሶስትዮሽ ትብብር ይፋ የተደረገው በኢትዮዽያ በግብርና፣ በአግሮ ኢንዱስትሪ፣ በታዳሽ ኃይል፣በዲጂታላይዜሽን የልህቀት ማዕከላትን የመመስረት ስራ የአርሶ እና አርብቶ አደሮችን እና የገጠር ነዋሪዎችን ሕይወት ለማሻሻል ልዩ ዕድል ይዞ መጥቷል።
ኢዜአ የተደራሽነት አድማሱን በማስፋት ከኢትዮጵያ አልፎ የአፍሪካ አስተማማኝ የዜና ምንጭ መሆን አለበት- አቶ ተስፋዬ ቤልጂጌ
Feb 18, 2024 398
አዲስ አበባ ፤ የካቲት 10/2016(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት /ኢዜአ/ የተደራሽነት አድማሱን በማስፋት ከኢትዮጵያ አልፎ የአፍሪካ አስተማማኝ የዜና ምንጭ መሆን አለበት ሲሉ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ ቤልጂጌ ገለጹ። የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትሩ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት /ኢዜአ/ ያስገነባውን ዘመናዊ የሚዲያ ኮምፕሌክስ ጎብኝተዋል። ከጉብኝቱ በኋላ በሰጡት አስተያየትም ኢዜአ ከኢትዮጵያም አልፎ በአፍሪካ የገዘፈ ታሪክና ስም ያለው ተቋም መሆኑን ገልጸዋል። በመሆኑም አዲስ ያስገነባው ዘመናዊ የሚዲያ ኮምፕሌክስ የተቋሙን ራእይና ተልእኮ ለማሳካት ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው ለኢትዮጵያ የሚዲያ ኢንዱስትሪ እድገትም ጥሩ መሰረት መሆኑን ጠቅሰዋል። የተገነባው የሚዲያ ኮምፕሌክስና እየተጠቀመ ያለው ቴክኖሎጂ ከዓለም ትላልቅ መገናኛ ብዙሃን ጋር የሚስተካከል መሆኑንም ገልጸዋል። በመሆኑም ኢዜአ በቋንቋ ብዝሃነትም ይሁን ተቋማዊ አቅም የተደራሽነት አድማሱን በማስፋት ከኢትዮጵያ አልፎ የአፍሪካ አስተማማኝ የዜና ምንጭ መሆን አለበት ነው ያሉት። በሁሉም ዘርፍ በሀገሪቷ የተከናወኑ የሪፎርም ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን ጠቅሰው ለሚዲያው የሪፎርም ስራም ኢዜአ ሁነኛ ማሳያ ነው ብለዋል። በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ስርአት እንዲጎለብት በማድረግ ረገድ የሚዲያ ሚና ወሳኝ መሆኑን የገለጹት አቶ ተስፋዬ፤ ኢዜአ ይህንን ሚናውን በመወጣትና ብሄራዊ መግባባት በመፍጠር የጀመራቸውን ስራዎች አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ገልጸዋል። በኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ልማት ተረጋግጦ የተጀመረው የብልጽግና ጉዞ እንዲሳካ በመስራት ረገድ ትልቅ ሀገራዊ ሃላፊነት ያለበት መሆኑንም አንስተዋል። ኢዜአ የስርጭትና ተደራሽነት አድማሱን በምስራቅ አፍሪካ ለማስፋት በኬንያ እና በጅቡቲ ቅርንጫፎችን ለመክፈት በዝግጅት ላይ ይገኛል። ከተመሠረተ 82 ዓመታት የሆነው አንጋፋው ኢዜአ ብሔራዊ መግባባት የመፍጠርና የአገር ገፅታ ግንባታ ተልዕኮውን ለማሳካት ዜና እና ዜና ነክ መረጃዎችን ተደራሽ በማድረግ ላይ ይገኛል።
የበለፀገች አፍሪካን እውን ለማድረግ ለአህጉራዊ ድንበር የለሽ ዲጂታላይዜሽን ትኩረት መስጠት ይገባል
Feb 17, 2024 346
አዲስ አበባ፤ የካቲት 9/2016(ኢዜአ)፦ በ2063 የበለፀገች አፍሪካን እውን ለማድረግ የተያዘውን ግብ ለማሳካት ለአህጉራዊ ድንበር የለሽ የቴክኖሎጂ ትስስርና ለአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ትኩረት መስጠት እንደሚገባ ተገለጸ። "የዲጂታላይዜሽን መስፋፋት ለአፍሪካ ትራንስፎርሜሽን" በሚል መሪ ሃሳብ ላይ ያተኮረ የመንግሥታትና የተቋማት መሪዎች ውይይት በዓድዋ ድል መታሰቢያ ፓን-አፍሪካ አዳራሽ ተካሂዷል። ፕሬዝዳንት ሣህለወርቅ ዘውዴ በዚህ ወቅት እንዳሉት፤ በፍጥነት እያደገ የመጣው የቴክኖሎጂ ምህዳር ዓለም ጂኦ-ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበረሰባዊ እና ባህላዊ ለውጦችን እንድታስተናግድ አስገድዷታል። አፍሪካም ለዲጂታልና ለቴክኖሎጂ ፈጠራ ትኩረት እንድትሰጥ ጫና ማሳደሩንም ጠቅሰዋል። አፍሪካ ዲጂታላይዜሽንን በማስፋፋት፣ ምርታማነትን በማሳደግ፣ ፈጠራን በማጎልበትና የሥራ ዕድልን በመጨመር ግዙፍ የኢኮኖሚ እድገት እንድታስመዘግብ ዕድል ይፈጥራል ነው ያሉት። በ2063 የምንመኛትን የበለፀገች አፍሪካ ለመፍጠር የዲጂታላይዜሽን መስፋፋት ጉልህ ሚና እንደሚኖረው ጠቅሰው፤ ከ2020 እስከ 2030 የሚተገበር አህጉራዊ የዲጂታል ሽግግር አጀንዳ ወደ ሥራ መግባቱን አውስተዋል። ኢትዮጵያም ከአህጉሪቱ እሳቤዎች ጋር የሚጣጣም ዲጂታል 2025ን ስትራቴጂ በማዘጋጀት ወደ ሥራ መግባቷን ጠቅሰዋል። በዚህም የቴሌኮም መሠረተ-ልማት ማስፋፋት፣ የኢንተርኔት ተደራሽነትና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ላይ ሰፋፊ ተግባራት እያከናወነች መሆኑን ገልፀዋል። በአፍሪካ አካታችና ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ የዲጂታል ሽግግርን ማፋጠን እንደሚገባም ጠቁመዋል። በውይይት መድረኩ ላይ በዲጂታል አፍሪካ ዙሪያ ሃሳባቸውን ያካፈሉት የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬህይወት ታምሩ፤ የተሻለ ነገን በዘላቂነት ለመገንባት የቴክኖሎጂ አካታችነትን ማረጋገጥ ይገባል ብለዋል። የአፍሪካ ሕብረት በአባል ሀገራት የሚተገበር ወሳኝ ስትራቴጂ መቅረጹን ጠቅሰው፤ ዛሬ ላይ በአህጉሪቱ 1 ነጥብ 4 ቢሊየን የሞባይል ተጠቃሚዎች እንዳሉና በ2030 1 ነጥብ 7 ቢሊየን ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልፀዋል። በተለይም የፋይናንስ የትምህርትና የጤና ልማት አካታችነትን ለማረጋገጥ የሞባይል ቴክኖሎጂን መጠቀም ተገቢ እንደሆነ ጠቁመዋል። በአፍሪካ ያልተነካውን የተፈጥሮ ኃብት ለማልማት የዲጂታል ተደራሽነት አስፈላጊ መሆኑን ገልፀዋል። በዓለም የኢኮኖሚ ፎረም የአፍሪካ ቀጣና የትግበራ ቡድን ተባባሪ ሊቀመንበር ፕሮፌሰር ላንድሪ ሲኜ፤ አፍሪካ የኢኮኖሚ እድገትና መዋቅራዊ ለውጥን በማረጋገጥ በዓለም ተፅዕኖ ፈጣሪ ለመሆን ለዲጂታል አሠራር ትኩረት መስጠት እንዳለባት ተናግረዋል። በአፍሪካ በርካታ አምራች ኃይል የመኖሩን ያህል የዲጂታል ልህቀት ያልዳበረበት ሥርዓተ-ምህዳር መኖሩንም ጠቅሰዋል። በመሆኑም ለዲጂታላይዜሸን የቀረቡና የላቁ አፍሪካውያንን ለመፍጠር ከመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ጀምሮ ማስተማር ይገባል ነው ያሉት። ይህም አምራች ኃይሉ በታዳጊነቱ የላቀ የቴክኖሎጂ ግንዛቤ እንዲኖረው ስለሚያደርግ ለኢኮኖሚ እድገት መፋጠን ወሳኝ እንደሆነም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ ቴክኖሎጂን በመጠቀም ሁሉን አቀፍ እድገትን ለማምጣት እየሰሩ ከሚገኙ ሀገራት መካከል ተጠቃሽ መሆኗንም ነው ፕሮፌሰሩ የተናገሩት። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ከፍተኛ አማካሪ ሰለሞን ካሳ፤ አፍሪካ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ (ሰው ሰራሽ አስተውሎት) ለውጥ ለማምጣት ኢትዮጵያ ሀገራዊ ሚናዋን ለመወጣት እየጣረች ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ዲጂታል መር ኢኮኖሚ ለመገንባት የካፒታል ገበያ፣ የዲጂታል ክፍያ ሥርዓትን ጨምሮ ትኩረት መስጠቷን ተናግረዋል። ያለንበት ዘመን የሰው ሰራሽ አስተውሎት እየተስፋፋ ያለበት ነው ያሉት አማካሪው፤ ይህ ዘርፍ በ2030 ለዓለም ኢኮኖሚ 12 ነጥብ 5 ትሪሊየን ዶላር እንደሚያበርክት ይጠበቃል ብለዋል። ሆኖም አሁን ባለው ሂደት አፍሪካ የቴክኖሎጂ ኢ-ፍትሃዊ ተጎጂ በመሆኗ፤ ሀገራት ከፈጠራና ቴክኖሎጂ በአግባቡ ለመጠቀም የተባበረ ጥረት እንዲያደርጉም ጠቁመዋል። የኦንአፍሪቅ የዲጂታል ክፍያ መፈጸሚያ ድርጅት መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ዳሬ ኦኮጁ በበኩላቸው፤ በአፍሪካ ቴክኖሎጂ ጥቅም ላይ ቢውል አህጉራዊ ብልፅግናን በአጭር ጊዜ ማረጋገጥ እንደሚቻል ጠቁመዋል። በአፍሪካ ለአነስተኛና መካከለኛ የቢዝነስ ተቋማት ዲጂታላይዜሽን መስፋፋት ድንበር የለሽ የቴክኖሎጂ ትስስርን ማጠናከር ተገቢ ነው ብለዋል።