ሳይንስና ቴክኖሎጂ
ኮሌጁ የተሻሻሉ የቡና፣ ፍራፍሬና ቅመማቅመም ዝርያ ችግኞችን የማላመድና የማስፋፋት ስራ እያከናወነ መሆኑን ገለጸ
Jul 10, 2024 799
ሚዛን አማን፤ ሀምሌ 3/2016 (ኢዜአ)፦የሚዛን ግብርና ቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ኮሌጅ በምርምር የተገኙ የተሻሻለ ዝርያ ያላቸው የቡና፣ፍራፍሬና ቅመማቅመም ችግኞችን እያላመደና እያስፋፋ መሆኑን አስታወቀ፡፡ በምርምር የተገኙ ምርጥ የፍራፍሬና የቡና ዝርያ ችግኝ ዝግጅት ሥራ ያለበት ደረጃን ለመገምገም ያለመ የመስክ ምልከታ ዛሬ በኮሌጁ ዘር ብዜት ጣቢያዎች ተካሂዷል።   የኮሌጁ ዲን አቶ ካሳሁን ናይክን በወቅቱ እንደገለጹት ኮሌጁ በግብርና ዘርፍ በምርምር የተገኙ ውጤቶችን በአካባቢው ለማስፋፋት እየሰራ ነው፡፡ ለዘንድሮ የክረምት ወራት የሚተከሉ ከ550 ሺህ በላይ ዝርያቸው የተሻሻለ ምርጥ የቡናና የፍራፍሬ ችግኞች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል። ከችግኞቹ ውስጥ 400 ሺህ ያህሉ በሽታ የሚቋቋሙና ምርታማ የቡና ችግኞች መሆናቸውን ጠቅሰው የቡና ችግኞቹ "የጌሻ ቡና"፣ "ሰባ አራት አርባ" እና "ሰባ አራት ሃምሳ አራት" የተሰኙ ምርጥ የቡና ዝርያ ያላቸው መሆናቸውን ጠቅሰዋል። "ችግኞቹን ለአርሶ አደሮች በማሰራጨት ምርትና ምርታማነቱ የተረጋገጠ ቡና እንዲለማ ይደረጋል" ብለዋል። ከቡና ባሻገር በሁለት ዓመት ውስጥ ምርት የሚሰጥ የአቡካዶ፣ ቁንዶ በርበሬ፣ ሻይ ቅጠል እንዲሁም ሌሎች ፍራፍሬዎችና ቅመማ ቅመሞችን የማላመድና የማስፋፋት ሥራ ላይ ትኩረት መደረጉን ገልጸዋል።   ዲኑ አክለውም ኮሌጁ የምርምር ሥራዎችን ከቴፒ ግብርና ምርምር ማዕከል ጋር በመተባበር እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል ። በማባዣ ችግኝ ጣቢያዎችም ከሀምሳ ለሚበልጡ ወጣቶች በስልጠና የታገዘ የሥራ ዕድል መፈጠሩን ጠቁመዋል። በኮሌጁ የቴክኖሎጂ ብዜትና ኢንተርፕራይዝ ልማት ምክትል ዲን ዋለልኝ ዓለምነህ በበኩላቸው ኮሌጁ የመንግስትን የልማት ፖሊሲ የተከተለ የልማት ሥራን ለማቀላጠፍ ጥረት እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል። የእንስሳትና ንብ እርባታ ሥራን ጨምሮ በምርምር የተደገፉ ተግባራትን በአርሶ አደሩ ማሳ በማላመድ እየተወጣ ያለውን ማኅበራዊ ኃላፊነት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል። " ኮሌጁ በቀጣይየራሱን ገቢ ለማመንጨት በሚያከናውናቸው ተግባራት ለበርካቶች የሥራ ዕድል በመፍጠር የቴክኖሎጂ ሽግግር ያደረጋል" ብለዋል። የቤንች ሸኮ ዞን ቡና፣ ሻይና ቅመማ ቅመም ጽህፈት ቤት ኃላፊ ወይዘሪት ወርቅነሽ ባድንስ ኮሌጁ የምርምር ውጤቶችን በአካባቢው ለማላመድ እያደረገ ያለው ጥረት የአርሶ አደሩን ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት ከፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል። የነባር ዝርያዎች ምርታማነት እያሽቆለቆለ መምጣቱን ጠቅሰው በቀጣይ በምርምር የተገኙ ዘሮችን ይበልጥ ለማስፋፋት ከኮሌጁ ጋር ተቀናጅተው እንደሚሠሩ አመላክተዋል። በኮሌጁ የተሻሻሉ የችግኝ ዘሮችን ማባዛት ላይ የሥራ ዕድል ከተፈጠረላቸው መካከል ወጣት ሙላቱ ዳባ ራሱን ለማስተዳደር የሚያስችል ገቢ እያገኘ መሆኑን ተናግሯል። በችግኝ ዝግጅት ሥራ ላይ ከተሰማራ አንድ ዓመት እንደሆነው ገልጾ ከገቢ ባሻገር ያዘጋጃቸው ችግኞች ለውጤት ሲበቁ ማየት እንደሚያስደስተው ገልጿል።   በችግኝ ጣቢያው የሥራ ዕድል የተፈጠረለት የኮሌጁ ተመራቂ ወጣት ዓለማየሁ መኮንን በበኩሉ የተሻለ ልምድና ክህሎት እያዳበረ መሆኑን ገልጿል። የሚዛን ግብርና ቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ስልጠና ኮሌጅ ከ1994 ዓ.ም ጀምሮ ተማሪዎችን በመቀበል የግብርና ባለሙያዎችን ከማፍራት ባሻገር በግብርናው ዘርፍ ምርምሮችን እያደረገ የሚገኝ ኮሌጅ ነው።  
ኢትዮ ቴሌኮም በዲጂታል ኢትዮጵያ ግንባታ ሂደት የመሪነት ሚናውን እየተወጣ ነው - ፍሬህይወት ታምሩ
Jul 10, 2024 407
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮ ቴሌኮም አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ገቢራዊ በማድረግ ለዲጂታል ኢትዮጵያ ግንባታ የመሪነት ሚናውን እየተወጣ መሆኑን ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ፡፡ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ የኩባንያውን የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም በተመለከተ ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም በ2016 በጀት ዓመት ሁሉንም ማህበረሰብ የሚያሳትፍ፤ የሀገሪቷን ሁለንተናዊ ዕድገት የሚያረጋግጥና ዓለም አቀፋዊ ነባራዊ ሁኔታን ታሳቢ ያደረገ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ሥራ መገባቱን ገልጸዋል። ከ2015 ጀምሮ ለሶስት ዓመታት በሚቆየው መሪ የዕድገት ስትራቴጂው የቴክኖሎጂ ልህቀትን ማረጋገጥ፣ ከፍተኛ አፈፃፀም ያለው ተቋም መገንባት፣ በአጋሮችና በደንበኞች ተመራጭ መሆን የትኩረት መስኮች መሆናቸውን አስታውሰዋል። በዚህም የዲጂታል ኢትዮጵያን ግንባታ እውን ማድረግ የሚያስችሉ ውጤቶች መገኘታቸውንና ስራው ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። ለአብነት የቴሌብር አገልግሎት ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን 2 ነጥብ 55 ትሪሊዬን ብር ግብይት መፈጸሙን አንስተዋል ፡፡ ቴሌብር ለዜጎች የሚሰጠውን አገልግሎት በማቀላጠፍ የዲጅታል ኢትዮጵያን ግንባታ እያገዘ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡ አሁን ላይ የቴሌ ብር ተጠቃሚዎች ቁጥር 47 ነጥብ 5 ሚሊዬን መድረሱንና በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ብቻ 1 ነጥብ 8 ትሪሊዬን ብር ግብይት መከናወኑን ነው የገለጹት፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም የ2016 በጀት ዓመት እቅዱን በስኬት ማጠናቀቁን የገለጹት ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ፤ 462 አዳዲስ የሞባይል ጣቢያዎች ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ተናግረዋል። ኢትዮ ቴሌኮም 86 ሚሊዮን ደንበኞችን ማስተናገድ የሚያስችል የሞባይል ኔትወርክ አቅም መገንባቱን በመጠቆም የ4G አገልግሎት 34 ነጥብ 6 በመቶ ደርሷል ብለዋል።   በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ124 ከተሞች የ4G አገልግሎት በመስጠት የ4G ተጠቃሚ ከተሞችን 424 ማድረስ መቻሉን ገልጸዋል። ከዚህም ባለፈ 132 የገጠር የሞባይል ጣቢያዎች ከ2G ወደ 3G አገልግሎት ማደጋቸውን ጠቅሰው፤ በአምስት ከተሞች የ5G አገልግሎት ማስፋፊያ መደረጉንና በሂደት ላይ ያሉ መኖራቸውን ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ቀደም የሞባይል ኔትወርክ ያልነበራቸውን 216 የገጠር ቀበሌዎች በኔትወርክ ማስተሳሰር መቻሉን ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ አስታውቀዋል። በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች በተከሰቱ ግጭቶች የወደሙ የቴሌኮም መሰረተ ልማቶችን በመጠገን መልሶ ወደ ስራ ማስገባት መቻሉን ተናግረዋል ፡፡ በዚህም ጉዳት የደረሰባቸውን 179 የቴሌኮም ጣቢያዎች እና 570 ኪሎ ሜትር የፋይበር ጥገና በማከናወን ህብረተሰቡ ዳግም የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዲሆን መደረጉን ገልጸዋል፡፡ በአጠቃላይ የሞባይል ኔትወርክ ተደራሽነት በቆዳ ስፋት 85 ነጥብ 4 ፤ በተጠቃሚዎች ደግሞ ከ99 በመቶ በላይ መድረሱን ጠቁመዋል፡፡ ኢትዮ ቴሌኮም የደንበኞችን ፍላጎት መሰረት ያደረጉ ምርትና አገልግሎቶችን ከማቅረብና ማህበራዊ ሃላፊነቱን ከመወጣት ባለፈ ለመንግስት ገቢ በማስገኘትም ሚናው የጎላ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በዚህም በተጠናቀቀው በጀት ዓመት 93 ነጥብ 7 ቢሊየን ገቢ በማግኘት የዕቅዱን 103 ነጥብ 6 በመቶ ማሳካት መቻሉን አስታውቀዋል፡፡    
መረጃዎችን  ለመሰበሰብ  የሚረዳ "ሃይ አልቲትዩድ ሳተላይት  ባሉን" ወደ አየር  ተለቀቀ  
Jul 10, 2024 285
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2016(ኢዜአ)፦ የስፔስ ሳይንስና ጂኦ ስፓሻል ኢኒስቲትዩት መረጃን ለመሰብሰብ የሚረዳ "ሃይ አልቲትዩድ ሳተላይት ባሉን " ወደ አየር ለቀቀ ። ሳተላይት ባሉንን የመልቀቅ ስነ ስርአት በሸገር ከተማ ሱሉሉታ ክፍለ ከተማ የተካሄደ ሲሆን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሽሩን ዓለማሁ (ዶ/ር)፣ የቦይንግ ኩባንያ የአፍሪካ ዳይሬክተር አምባሳደር ሄኖክ ተፈራ እንዲሁም ተማሪዎች ተገኝተዋል ፡፡ ኢኒስቲትዩቱ ከቦይንግ እና ፋሴሳ ከተሰኙ ድርጅቶች ጋር በመተባበር "ፓዝ ወይ ቱ ስፔስ' በሚል መሪ ሃሳብ ያሰለጠናቸውን ተማሪዎች በማስመረቅ ላይ ነው፡፡ ተማሪዎቹ ከ 16 እስከ 20 ዓመት ዕድሜ ክልል ውስጥ የሚገኙ ሲሆን "ሃይ አልቲትዩድ ሳተላይት ባሉን " ዲዛይንና ግንባታ ዙሪያ ለአምስት ወራት ስልጠና የወሰዱ ናቸው፡፡ ተማሪዎቹ በስልጠናው የቀሰሙትን እውቀት ተጠቅመው የሰሩትን ሃይ አልቲትዩድ ሳተላይት ባሉን የሙከራ ውጤት አቅርበዋል፡፡
በኢትዮጵያ የ4G አገልግሎት ተጠቃሚ ከተሞች 424 ደርሰዋል
Jul 10, 2024 216
አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 3/2016(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ የ4G አገልግሎት ተጠቃሚ ከተሞች 424 መድረሳቸውን የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ ገለጹ። ዋና ሥራ አስፈፃሚዋ የኩባንያውን የ2016 በጀት ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም በተመለከተ ለመገናኛ ብዙኃን መግለጫ ሰጥተዋል። በመግለጫቸውም በ2016 በጀት ዓመት ሁሉንም ማህበረሰብ የሚያሳትፍ፤ የሀገሪቷን ሁለንተናዊ ዕድገት የሚያረጋግጥና ዓለም አቀፋዊ ነባራዊ ሁኔታን ታሳቢ ያደረገ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ሥራ መገባቱን ገልጸዋል። ከ2015 ጀምሮ ለሶስት ዓመታት በሚቆየው መሪ የዕድገት ስትራቴጂው የቴክኖሎጂ ልህቀትን ማረጋገጥ፣ ከፍተኛ አፈፃፀም ያለው ተቋም መገንባት፣ በአጋሮችና በደንበኞች ተመራጭ መሆን የትኩረት መስኮች መሆናቸውን አስታውሰዋል። በዚህም የዲጂታል ኢትዮጵያን ግንባታ እውን ማድረግ የሚያስችሉ ውጤቶች መገኘታቸውን ጠቅሰው ስራው ተጠናክሮ መቀጠሉን ገልጸዋል። በ2016 በጀት ዓመትም 462 አዳዲስ የሞባይል ጣቢያዎች ተገንብተው አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን ተናግረዋል። ከዚህም ባለፈ 132 የገጠር የሞባይል ጣቢያዎች ከ2G ወደ 3G አገልግሎት ማደጋቸውን ገልጸዋል። ኢትዮ ቴሌኮም 86 ሚሊዮን ደንበኞችን ማስተናገድ የሚያስችል የሞባይል ኔትወርክ አቅም መገንባቱን ገልጸው፣ የ4G አገልግሎት 34 ነጥብ 6 በመቶ ደርሷል ብለዋል። በተጠናቀቀው በጀት በ124 ከተሞች የ4G አገልግሎት በመስጠት የ4G ተጠቃሚ ከተሞችን ወደ 424 ማድረስ መቻሉን ገልጸዋል። በአምስት ከተሞች የ5G አገልግሎት ማስፋፊያ መደረጉን ጠቅሰው ሌሎች በሂደት ላይ ያሉ መኖራቸውንም ጠቁመዋል። ከዚህ ቀደም የሞባይል ኔትወርክ ያልነበራቸውን 216 የገጠር ቀበሌዎች በኔትወርክ ማስተሳሰር ተችሏል ብለዋል። የሞባይል ኔትወርክ ተደራሽነት በቆዳ ስፋት 85 ነጥብ 4፤ በተጠቃሚዎች ደግሞ ከ99 በመቶ በላይ ደርሷል ብለዋል። የዲጂታል ኢትዮጵያን እቅድ ዕውን ለማድረግ እየተደረገ ያለው ጥረት በጥሩ ሂደት ላይ መሆኑን ጠቅሰው የ93 ነጥብ 7 ቢሊየን ገቢ የተገኘበት መሆኑንም አንስተዋል።
በትግራይ ክልል የሚገኙ ነዳጅ ማደያዎች በዘመናዊ የክፍያ ስርዓት አገልግሎት እንዲሰጡ ሊደረግ ነው
Jul 6, 2024 289
መቀሌ ፤ ሰኔ 29/2016(ኢዜአ)፦ በትግራይ ክልል የሚገኙ የነዳጅ ማደያዎች ከሐምሌ 1 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ በዘመናዊ የክፍያ ስርዓት አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚደረግ ተገለጸ። ከተቀመጠው አሰራር ውጭ ሌላ አማራጭ የሚጠቀሙ ነዳጅ ማደያዎች ከተገኙ ከስራው እንደሚታገዱ ዛሬ በተሰጠው መግለጫ ተመልክቷል። መግለጫውን የሰጡት የትግራይ ክልል የጊዜያዊ አስተዳደሩ የትራንስፖርትና መገናኛ ቢሮ፣ የጊዜያዊ አስተዳደር የንግድ ኤጀንሲ እና በኢትዮ ቴሌኮም የሰሜን ሪጅን ናቸው። በክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የንግድ ኤጀንሲ የንግድ ውድድርና የሸማቾች ብቃት ዳይሬክተር አቶ ካሳሁን ክንደያ እንደገለጹት፤ ከሐምሌ 1 ቀን 2016 ዓ.ም ጀምሮ ነዳጅ የሚጠቀሙ ተሽከርካሪዎችና ጀኔሬተር ባለቤቶች የነዳጅ ክፍያ ስርዓት በቴሌ ብር እንዲገለገሉ ይሆናል። ዘመናዊ አሰራሩ በክልሉ በሚገኙ 60 ነዳጅ ማደያዎች ላይ ተግባራዊ እንደሚሆን አስታውቀዋል። የነዳጅ መቅዳትና የክፍያው ስርዓት ዘመናዊ የማድረግ ስራ ነዳጅ በጥቁር ገበያ እንዳይሸጥ ለመከለከልና የተሳለጥ አገልግሎት እንዲኖር ለማስቻል መሆኑን ተናግረዋል። በነዳጅ አጠቃቀም ዙሪያ የነበረው ህገ ወጥ ስራ ለግለሰቦች መበልፀገያ እንጂ ለህዝባችን የጠቀመ አይደለም ብለዋል። ዘመናዊ የነዳጅ ግብይት አሰራር ተግባራዊ በማድረግ አገልግሎቱን የተቀላጠፈ እናደርጋለን ያሉት ደግሞ በክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር የትራንስፖርትና መገናኛ ቢሮ ሀላፊ አቶ ታደለ መንግስቱ ናቸው። በኢትዮ ቴሌኮም የሰሜን ሪጅን ዳይሬክተር አቶ ሙሉ ወልደስላሰ በበኩላቸው፤ ነዳጅ አሞላልና ክፍያ አፈፃፀም ላይ ያለው ኋላ ቀር አሰራር ተቀይሮ ፈጣንና ፍትሃዊ አገልግሎት በቴሌ ብር ለመስጠት ዝግጅት መደረጉን አስታውቀዋል። መብረት የመጥፋትና ሌሎች ተመሳሳይ ችግሮች እንዳይፈጠሩ ለመፍታት የሚያስችል ዝግጅት መደረጉንም ገልጸዋል።
ዩኒቨርሲቲው ሳይንስና በቴክኖሎጂ ዘርፍ የጀመራቸው የምርምር ስራዎች አገርን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ የሚያግዙ ናቸው -አለሙ ስሜ (ዶ/ር)
Jul 6, 2024 445
አዳማ ፤ ሰኔ 29/2016 (ኢዜአ)፡- የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ በሳይንስና በቴክኖሎጂ ዘርፍ የጀመራቸው የምርምር ስራዎች አገርን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ የሚያግዙ መሆናቸውን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። ዩኒቨርሲቲው በተለያዩ የትምህርት መስኮች በመጀመሪያ፣ በሁለተኛና ሶስተኛ ዲግሪ ያሰለጠናቸውን 1 ሺህ 102 ተማሪዎች ዛሬ አስመረቋል።   በምረቃው ስነ-ስርዓት ላይ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር)፣ የአየር ሃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ እና ሌሎችም እንግዶች ተገኝተዋል። በዚሁ ወቅት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዓለሙ ስሜ (ዶ/ር) ፣ ዩኒቨርሲቲው አጠቃላይ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ረገድ የጀመራቸውን የምርምር ስራዎች አገርን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ የሚያግዙ መሆናቸውን ተናግረዋል።   በሳይንስና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ብቁ፣ ተወዳዳሪና ዓለም አቀፍ ተቀባይነት ያለውን የሰው ሃይል ማፍራት የበለጠ መጠናከር እንዳለበትም አመልክተዋል። ዩኒቨርሲቲው በምስራቅ አፍሪካ የሳይንስና ቴክኖሎጂ የልህቀት ማዕከል ለመሆን ያስቀመጠውን ግብ እንዲሳካም ሁሉም ድጋፍና ትብብር ማድረግ እንዳለበት ነው የተናገሩት።   የአዳማ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶክተር ለሚ ጉታ በበኩላቸው፤ ዩኒቨርሲቲው በሳይንስና ቴክኖሎጂ ብቁ የሰው ሃይል ለማፍራት ተማሪዎችን አወዳድሮ በመቀበል በተለያዩ የሙያ መስኮች እያሰለጠ ይገኛል ብለዋል። በተለይም የህዋ ሳይንስ ምርምር፣ የተለያዩ የኢንጂነሪንግ ዘርፎችን ጨምሮ ስምንት የልህቀት ማዕከላት በመክፈት የአገሪቷ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት ስራዎች በምርምር ለመደገፍ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል።          
የሰው ሰራሽ አስተውሎት የመጪውን ዓለም መጻዒ ዕድል የሚወስን በመሆኑ ወጥ እሳቤ ይዘን መስራትና መከተል አለብን- ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)
Jul 4, 2024 366
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 27/2016(ኢዜአ)፦ የሰው ሰራሽ አስተውሎትና መሰል የዘመኑ ቴክኖሎጂዎች የመጪውን ዓለም መጻዒ ዕድል የሚወስኑ በመሆኑ ወጥ እሳቤ ይዘን መስራት መከተልና በሰው ሃይል ልማት ላይ በትኩረት መስራት አለብን ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር)፤ በሀገራዊ ወቅታዊ ጉዳዮችና ሌሎችም ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማብራሪያቸው ዓለም በአዳዲስ ፈጠራና ቴክኖሎጂ ዘርፎች በማይገመት ፍጥነት እየተለወጠ ነው ብለዋል። ለአብነትም በሰው ሰራሽ አስተውሎት፣ በኮኔክቲቪቲ፣ በባዮ ምህንድስና፣ በስፔስ ቴክኖሎጂ እና መሰል የዘመን ስልጣኔ በፍጥነት እየተራመደ መሆኑን ገልጸዋል። ከዚህ ፍጥነት ጋር ትውልዱ እንዲራመድ ለማድረግ በዘመኑ ቴክሎኖጂዎች ሽግግር ላይ መስራት ይገባል ብለዋል። ለአብነትም የሮቦቲክስ ቴክኖሎጂ ልማዳዊ የሰው ልጅ አካሄዶችን ሙሉ በሙሉ በአዳዲስ ቴክኖሎጂዎች እየተኩ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህን ስጋት ተገንዝቦ ነገን ታሳቢ ያደረገ ስራ መስራት እንደሚጠይቅ ገልጸዋል። የዓለም ፍጥነት እጅግ አስፈሪ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዘመኑን በዋጁ የሰው ሰራሽ አስተውሎትና መሰል ቴክኖሎጂዎች ላይ ካልሰራን በምርት ተወዳዳሪ ሆኖ መቀጠል አይቻልም ብለዋል። ሰው ሰራሽ አስተውሎት እና መሰል የዘመኑ ቴክኖሎጂዎች የመጪውን ዓለም መጻዒ ዕድል የሚወስኑ በመሆኑ ወጥ እሳቤ ይዘን መከተልና በሰው ሃይል ልማት ላይ በትኩረት መስራት ይጠበቅብናልም ነው ያሉት በሰው ሰራሽ አስተውሎትና መሰል የዘመኑ ቴክኖሎጂዎች ላይ ልጆች መሰረታዊ ዕውቅት እንዲይዙ ነገን ማየትና በቴክኖሎጂ ላይ ወጥ እሳቤ ይዞ መከተል ያስፈልጋልም ብለዋል። በመሆኑም ከጥርጣሬና ሽኩቻ ይልቅ የሀገርን አንድነት ማጽናት የሁላችንም የጋራ አቋም አድርገን መስራት አለብን ሲሉ አስገንዝበዋል።  
በታዳሽ ኃይል የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ለማስፋፋት እየተሰራ ነው
Jul 3, 2024 499
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 26/2016(ኢዜአ)፦ በታዳሽ ኃይል ለሚሰሩ ተሽከርካሪዎች ስታንዳርድ እንዲዘጋጅ በማድረግ በአገሪቱ እንዲስፋፉ እየተሰራ መሆኑን የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ገለጹ። በአዲስ አበባ ሚሊኒየም አዳራሽ ከሰኔ 26 እስከ 28/2016 ዓ.ም የሚካሄደው ኢትዮ-ኦቶሞቲቭ፣ የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ኤክስፖን የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) ዛሬ መርቀው ከፍተውታል።   በኤክስፖው በኦቶሞቲቭ የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ዘርፍ የተሰማሩ ዓለም አቀፍ የተሽከርካሪ አምራቾች፣ መገጣጠሚያ፣ ወኪል አስመጪዎችና በዘርፉ የተሰማሩ አቅራቢዎች ተሳትፈዋል። በአየርና በየብስ ትራንስፖርት የተሰማሩ ኩባንያዎችና የሎጀስቲክስ አስተላላፊዎችም እየተሳተፉ ነው። የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር አለሙ ስሜ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ፤ በኤክስፖው የዘርፉ ተዋናዮች የቴክኖሎጂ ፈጠራ ምርትና አገልግሎታቸውን እንዲያስተዋውቁ ታልሞ የተዘጋጀ ነው ብለዋል። የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ዘርፍ ለአገር ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ መሳለጥ የሚጠበቅበትን አይተኬ ሚና መወጣት የሚያስችለውን የአሰራር ማሻሻያ ተድርጎ እየተሰራበት እንደሚገኝም ገልጸዋል። በዚህም በታዳሽ ኃይል የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን በማስገባት ለረጅም ዓመታት ሲያገለግሉ የቆዩ ተሽከርካሪዎችን መተካት የሚስችል ስትራቴጂክ ፖሊሲ ሥራ ላይ እንዲውል መደረጉን ተናግረዋል በኢትዮጵያም ዘመናዊ ትራንስፖርት አገልግሎት ተደራሽነትን ለማስፋት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በትብብር እየተሰራ እንደሚገኝ አንስተዋል። ባለፉት አምስት ዓመታትም ወጥ የሆነ የአሸከርካሪ ምዘና በማዘጋጀት የዜጎችን ህይወት እየቀጠፈ የሚገኘውን የትራፊክ አደጋ ለመቀነስ እየተሰራ መሆኑንም አስረድተዋል። በታዳሽ ኃይል ለሚሰሩ ተሽከርካሪዎች ስታንዳርድ እንዲዘጋጅ በማድረግ በአገሪቱ እንዲስፋፉ እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል።   የበላይነህ ክንዴ ግሩፕ ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር ሰጠኝ እንግዳው፤ ኤክስፖው ኩባንያቸው የሚገጣጥማቸውን በታዳሽ ኃይል የሚሰሩ ተሽከርካሪዎችን ለማስተዋወቅ ዕድል የፈጠረ ነው ብለዋል። በኤክስፖው ላይ ወጭ ቀጣቢና የአየር ብክለትን ለመቀነስ የሚያስችሉ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን በአውደ ርዕዩ እያስተዋወቁ መሆናቸውን ገልፀዋል። አጠቃላይ የትራፊክ አደጋ መቀነስ ቴክኖሎጂ አስመጪው ዑመር ያሲን፤ የትራፊክ አደጋን መቆጣጠር የሚያስችሉ አዳዲስ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ወደአገር ቤት በማስገባት እያስተዋወቁ መሆኑን ገልጸዋል።  
የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጠና የዲጂታል ግብይት ፕሮቶኮል ለዲጅታል የንግድ ዘርፍ ሰፊ እድል የሚፈጥር ነው
Jul 3, 2024 324
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 26/2016(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጠና የዲጂታል ግብይት ፕሮቶኮል ለዲጅታል የንግድ ዘርፍ ሰፊ እድል የሚፈጥር መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ገለጸ። በሚኒስቴሩ እና የኢትዮጵያ የአይ ሲቲ ማኅበር ትብብር የተዘጋጀው በአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣና ስምምነት የዲጂታል ግብይትን ለማካተት በሚያስችለው ፕሮቶኮልና ኢ-ኮሜርስ ላይ ያተኮረ አውደ- ጥናት ተካሂዷል።   በአውደ-ጥናቱ ላይ ንግግር ያደረጉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ይሹሩን አለማየሁ(ዶ/ር)፤ የዓለም የግብይት ሂደት በፍጥነት ወደ ዲጂታል መቀየሩን ገልፀዋል። በዚህ ረገድ የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና የዲጂታል ግብይት ፕሮቶኮልም ለአህጉራዊ የምጣኔ ኃብት እድገት ጥሩ መሠረት የሚያኖር ነው ብለዋል። የአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጠና የዲጂታል ግብይት ፕሮቶኮል ለዲጅታል የንግድ ዘርፍ ሰፊ እድል የሚፈጥር መሆኑንም ገልጸዋል። በመሆኑም በአፍሪካ ነፃ የንግድ ቀጣና የአይ ሲቲ ዘርፉን የላቀ ፋይዳና ተጠቃሚነት እውን ለማድረግ አስፈላጊው ድጋፍ ይደረጋል ሲሉ አረጋግጠዋል። በሚኒስቴሩ የዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት መሪ ሥራ አስፈጻሚ ስዩም መንገሻ፤ የዲጂታል 2025 ስትራቴጂን መሠረት በማድረግ በአይ ሲቲ ዘርፍ የተሰማሩ ድርጅቶችን ለመደገፍ የተለያዩ ሥራዎች እየተከናወኑ ነው ብለዋል። በግሉ ዘርፍ በሚነሱ ጥያቄዎች ላይ በመመስረት አሠራሮች መዘርጋታቸውንም ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ የአይ ሲቲ ማኅበር ፕሬዝዳንት ይልቃል አባተ፤ አውደ-ጥናቱ በያዝነው ዓመት የካቲት ወር ላይ በጸደቀው የአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣና የዲጂታል ግብይት ፕሮቶኮል አባሪዎች ላይ ለመምከር የተዘጋጀ ነው ብለዋል።  
የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የምርምር ውጤቶች ዓለም አቀፍ የባለቤትነት መብት እንዲያገኙ እየተሰራ ነው
Jul 1, 2024 360
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/2016 (ኢዜአ)፦ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ምርምር ውጤቶች ዓለም አቀፍ የባለቤትነት መብት እንዲያገኙ እየተሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና ገለጹ። በኢንስቲትዩቱ የበለፀጉ አራት የፈጠራ ውጤቶች ከኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለሥልጣን የባለቤትነት (ፓተንት) መብት ተሰጥቷቸዋል።   የባለቤትነት መብት የተሰጣቸው በሰው ሰራሸ አስተውሎት ቴክኖሎጂ መሠረት ያደረጉ የስኳር በሽታና፣ የጡት ካንሰር ዓይነቶችን የሚለይ፣ የህፃናት የቆዳ በሽታ ልየታ እና የቡና ቅጠል በሽታ የሚለይባቸው ናቸው። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር ወርቁ ጋቸና፤ ኢንስቲትዩቱ የተለያዩ የምርምር እና የልማት ሥራዎችን እያከናወነ ስለመሆኑ ተናግረዋል። በዛሬው ዕለት የባለቤትነት (ፓተንት) መብት የተሰጣቸው የምርምር ሥራዎችም የዚሁ ጥረት አካል መሆናቸውን ጠቅሰዋል። በቀጣይ የምርምር ሥራዎቹን ወደ ተግባር ማስገባቱ እንዳለ ሆኖ የተለያዩ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ የምርምር ሥራዎች ከሀገር ውስጥ ባለፈ ዓለም አቀፍ የባለቤትነት መብት እንዲያገኙ እየተሰራ ነው ብለዋል። የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ወልዱ ይመስል፤ በበኩላቸው የአዕምሮ ንብረት ጉዳይ የቀጣይ ዘመን የውድድር ዘርፍ ስለመሆኑ ገልጸዋል።   የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዘርፍ የቀጣይ ትውልድ የውድድር ብቃት ለማሳደግ ጠቃሚ በመሆኑ የላቀ የእውቀት ጥበቃ እንደሚደረግለት አስረድተዋል። የኢትዮጵያ አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት በሰው ሰራሽ አስተውሎት በምርምር እውቀትን አዳብሮ ባለቤትነት (ፓተንት) መብት ማስመዝገቡ የሚበረታታና ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት መሆኑን ጠቁመዋል።   የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ኢንስቲትዩት ምክትል ዋና ዳይሬክተር ታዬ ግርማ (ዶ/ር)፤ የባለቤትነት (ፓተንት) መብት የእውቅና ሰርቲፊኬት የተሰጣቸው የምርምር ውጤቶች በሰው ሰራሸ አስተውሎት ቴክኖሎጂ መሰረት ያደረጉ መሆናቸውን አብራርተዋል። እነዚህም የስኳር በሽታና፣ የጡት ካንሰር ዓይነቶችን የሚለይ፣ የሕፃናት የቆዳ በሽታ እና የቡና ቅጠል በሽታ ልየታ የሚያደርጉ የምርምር ግኝቶች መሆናቸውን ዘርዝረዋል።    
የፈጠራ ውጤቶች በአገራዊ የልማት እንቅስቃሴ ውስጥ የሚኖራቸውን ድርሻ ለማሳደግ የሚደረጉ ድጋፎች ተጠናክረው ቀጥለዋል
Jul 1, 2024 288
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/2016(ኢዜአ)፦የፈጠራ ውጤቶች ጥራታቸውን የጠበቁ፣ ተወዳዳሪ ሆነው በአገራዊ የልማት እንቅስቃሴ ውስጥ የሚኖራቸውን ድርሻ ለማሳደግ የሚደረጉ ድጋፎች ተጠናክረው መቀጠላቸው ተገለጸ። 14ኛው ከተማ አቀፍ የቴክኒክና ሙያ ሳምንት "ቴክኒክና ሙያ ለዘላቂ ሰላም" በሚል መሪ ኃሳብ ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ ተካሂዷል።   በኤግዚቢሽንና ባዛሩ ላይ ከተለያዩ የሙያና ቴክኒክ ተቋማት የተውጣጡ ወጣቶች የፈጠራ ውጤቶቻቸውን ይዘው ቀርበዋል። የኢዜአ ሪፖርተር የፈጠራ ውጤቶቻቸውን ይዘው የቀረቡ ወጣቶችን ተዘዋውራ አነጋግራለች። አስተያየት ሰጪዎቹ መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ልዩ ትኩረት ቴክኒክና ሙያ ተቋማት ብቁ ባለሙያዎችን ከማፍራት ባለፈ በሀገር የልማት እንቅስቃሴ ላይ ምርትና ምርታማነትን ማሳደግ የሚችሉ የፈጠራ ውጤቶችን በማበርከት የጎላ አስተዋጽዖ እያበረከቱ መሆኑን ተናግረዋል። ከአስተያየት ሰጪዎቹ መካከል የጋራዥ ባለሙያ የሆነው ሐብታሙ አበራ፣ ከልጅነቱ አንስቶ አዳዲስ የፈጠራ ውጤቶችን የመሞከር ዝንባሌ እንዳለው ይናገራል። ይህን ዝንባሌውን በቴክኒክና ሙያ ትምህርት በማዳበር አሁን ላይ ዘመኑ ያፈራው የተሽከርካሪ ሞዴል ሠርቶ ማቅረቡን ነው የሚያስረዳው። የፈጠራ ውጤቶችን መሥራት በብዛትና በጥራት ለማምረት የቦታና የግብዓት አቅርቦት ችግሮች መኖራቸውን ጠቁመው፤ በዚህ ረገድ የሚደረጉ ድጋፎች ሊጠናከሩ ይገባል ብለዋል።   የአቃቂ ፖሊቴክኒክ የቴክኖሎጂ ባለሙያ አበራ ደሳለኝ፤ ከዶሮ ጀምሮ ለበጎች፣ ለፍየሎች፣ ለከብቶችና ለተለያዩ እንስሳት ምግብን በሚፈልጉት መጠን ቆራርጦ ማቅረብ የሚችል ቴክኖሎጂ አቅርቧል። ቴክኖሎጂው የግብርናውን ዘርፍ ለማሳለጥ ትልቅ አቅም እንደሚሆን ገልፆ፤ መንግሥት ለፈጠራ ሥራ ባለሙያዎች የሚያደርገውን ድጋፍ እንዲያጠናክር ጠይቋል።   የጄኔራል ዊንጌት ፖሊቴክኒክ ኮሌጅ የ2016 ዓ.ም ተመራቂው ወጣት ዳግም ጋርጠው፤ በአገሪቱ በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ አደጋ ምክንያት የአካል ጉዳት የደረሰባቸው ዜጎች ራሱ መመገብ የሚችል አዲስ ሮቦት መፍጠር ችሏል። ይህ አዲስ የፈጠራ ሥራው የብዙ ኢትዮጵያውያንን ችግር በመፍታት የዜጎችን ችግር በማቃለል ኃላፊነትን መወጣት እንደሚያስችል ገልጿል።   ይህን አዲስ የፈጠራ ውጤት ለማኅበረሰቡ ተደራሽ ለማድረግ ድጋፍ እንደሚያስፈልግ ገልፆ፤ በዘርፉ የሚደረጉ ድጋፎች እንዲጠናከሩ ጥሪ አቅርቧል። የአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ የቴክኖሎጂ ምርምርና ሽግግር ዳይሬክተር ሲሳይ ቶልቻ በበኩላቸው፤ የቴክኒክና ሙያ ተቋማት ብቁ ባለሙያዎችን ከማፍራት ባለፈ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ የሚችሉ ቴክኖሎጂዎችን ከመፍጠር አኳያም እመርታ እያስመዘገቡ ነው ብለዋል።   አሁን ላይ የቴክኒክና ሙያ ተቋማትን በተለያዩ ዘርፎች የተሰማሩ የፈጠራ ውጤቶችን ይዘው የሚቀርቡ ወጣቶች በማፍራት ለአገር ወሳኝ የሚባሉትን ቴክኖሎጂዎችን በማፍራት ረገድ የማይናቅ ሚናን እየተጫወቱ ነው ብለዋል። በመሆኑም በአዳዲስ የፈጠራ ባለሙያዎች እየተሰሩ የሚቀርቡ አዲስና የተቀዱ ቴክኖሎጂዎች ወደ ሥራ ገብተው የሚፈለገውን ለውጥ ለማምጣት በዘርፉ የሚደረጉ ዘርፈ-ብዙ ድጋፎች ተጠናክረው መቀጠላቸውን ነው ያረጋገጡት።    
የኦቶሞቲቭ ትራንስፖርት አውደ ርዕይ በአዲስ አበባ ሊካሄድ ነው  
Jun 28, 2024 322
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2016 (ኢዜአ)፦የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር በትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ዘርፍ እንዲሁም በኦቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ ላይ ያተኮረ ኦቶሞቲቭ ትራንስፖርት አውደ ርዕይ በአዲስ አበባ ሊያካሂድ ነው። አውደ ርዕዩ ከሰኔ 26 እስከ 28 ቀን 2016 ዓ.ም በሚሊኒየም አዳራሽ ይካሄዳል ተብሏል። የትራንስፖርትና ሎጅስቲክስ ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሥራ አስፈጻሚ አመለወርቅ ሕዝቅኤል በዚሁ ጊዜ፣ ኤክስፖው በትራንስፖርትና በኦቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው ዘርፍ እየተሰሩ ያሉ ዋና ዋና ተግባራት ለማስተዋወቅ ያለመ ነው ብለዋል። አውደ ርዕዩ በዘርፉ የመጡ ለውጦችን ለማሳየትና ልምድ ለመለዋወጥ ትኩረት ማድረጉንም አብራርተዋል። በተለይም ሀገሪቱን ለከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ወጪ እየዳረገ የሚገኘውን የነዳጅ ፍጆታ ለማቅለል መንግሥት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ከቀረጥ ነጻ እንዲገቡ እያደረገ መሆኑን በማንሳት በአውደ ርዕዩ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችም ለዕይታ እንደሚቀርቡ ጠቁመዋል። በተጨማሪም ለኦቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው የሚውሉ የመለዋወጫ እቃዎችም ለእይታ እንደሚቀርቡ ጠቅሰዋል። አውደ ርዕዩ የዘርፉን ባለድርሻ አካላት አርስ በእርስ በማስተሳሰር ዘርፉን ለማዘመን የሚያስችሉ የቴክኖሎጂ የፈጠራ ውጤት ያላቸው ግለሰቦችና ተቋማት የፈጠራ ውጤታቸውን እንዲያሳዩ እድል የሚፈጥር መሆኑንም ተናግረዋል። በአውደ ርዕዩ የኦቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ የተሰማሩ ኩባንያዎች፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማትና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ይሳተፋሉ ተብሏል። አውደ ርዕዩን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር አውቶ ቴክ ከተሰኘ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ጋር በመተባበር እንዳዘጋጀው ተጠቅሷል።      
የስማርት ካምፓስ ፕሮጀክት ለትምህርት ጥራት እንዲሁም ለምርምርና ለአገልግሎት ልህቀት አጋዥ ነው - ሣሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር)
Jun 27, 2024 303
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2016(ኢዜአ)፦የስማርት ካምፓስ ፕሮጀክት ዩኒቨርሲቲው ለጀመረው የትምህርት ጥራት፣ የምርምርና አገልግሎት ልህቀት አጋዥ መሆኑን የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሣሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) ገለፁ። ኢትዮ-ቴሌኮምና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስማርት ካምፓስ ፕሮጀክት መተግበር የሚያስችላቸውን ሥምምነት አድርገዋል።   ሥምምነቱን የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) ፈርመውታል። ሥምምነቱ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስማርት መማሪያ ክፍሎች እና የተለያዩ ዘመናዊ ሶሉሽኖች ለማቅረብ እንደሚያስችል ተገልጿል። ሥምምነቱ የተለያዩ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች የተሟሉለት የትምህርት ጥራትና አካታችነትን ለማረጋገጥ፣ የትምህርት መረጃዎችን በቀላሉ ለማግኘት፣ የቤተ-ሙከራ ፍተሻዎችን በተሻለ ተሞክሮ ለማከናወን፣ የምዘና ፈተናዎችን ለመስጠት፣ ለማረምና ውጤቶችን ወዲያውኑ ለማሳወቅ የሚያስችል ስማርት የመማሪያ ክፍሎችን መገንባት ያስችላል ተብሏል። የስድስት ኪሎ ካምፓስ ግቢ የመግቢያ በሮች፣ ዋና ዋና የአስተዳደር ህንጻዎች፣ ሙዚየም፣ ካፍቴሪያዎች፣ የቤተ-መጽሐፍት፣ የተማሪዎችና የውጪ ሀገር ዜጎች የመኖሪያ ህንጻ ሰላማዊ እንቅስቃሴና ደህንነት ለመከታተል የሚያስችል የሲሲቲቪ ካሜራ፣ የመቆጣጠሪያ ማዕከልና የካምፓስ ፋይበር ኔትወርክ ዝርጋታና ተዛማጅ የመሰረተ ልማት ግንባታ የሚያካትት መሆኑ ተነስቷል። ሥምምነቱ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ህክምና ፋኩሊቲ የጥቁር አንበሳ አጠቃላይ ስፔሻላይድ ሆስፒታል የህክምና አገልግሎት ክፍያን በቴሌብር መፈጸም የሚያስችል ስትራቴጂያዊ አጋርነት መሆኑን ተጠቅሷል። በተጨማሪም የቅድመ ህክምና ገንዘብ ተቀማጭ (deposit)ና የድህረ ህክምና ቀሪ ገንዘብ ተመላሽ (refund) ማድረግና ሆስፒታሉ አሰራሩን በማዘመን አስተዳደራዊ ወጪዎች በመቀነስ ጉልህ ፋይዳ እንደሚኖረው ተመላክቷል። የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዝዳንት ሣሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ሥምምነቱ ዩኒቨርሲቲው የጀመረውን የለውጥ ሥራ የሚያግዝ ነው። በተለይም የስማርት ካምፓስ ፕሮጀክት ዩኒቨርሲቲው ለጀመረው የትምህርት ጥራትና ለምርምርና ለአገልግሎት ልህቀት አጋዥ እንደሆነ ተናግረዋል። ሥምምነቱ የትምህርት ጥራትን ከማስጠበቅ በላይ ዩኒቨርሲቲው በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆን የሚያግዝ መሆኑንም ጠቁመዋል። የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩ በበኩላቸው ኩባንያው ዲጂታል ኢትዮጵያን ራዕይ ለማሳካት በትኩረት እየሰራ ነው ብለዋል።   በዚህም ዘመኑ ያፈራቸውን የቴሌኮም መሰረተ ልማቶች በመገንባት ተደራሽ እያደረገ እንደሚገኝ ገልጸዋል። ጎን ለጎንም የዛሬውን ጨምሮ የተቋማትን አሰራር የሚያዘምን የዲጂታል አገልግሎቶችን በማቅረብ ላይ መሆኑን ተናግረዋል። ሥምምነቱ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን የሚሰጠውን አገልግሎት ውጤታማ ለማድረግ እንደሚያስችለው አስረድተዋል።    
ኢትዮ-ቴሌኮምና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስማርት ካምፓስ ፕሮጀክት ለመተግበር የሚያስችል ሥምምነት አደረጉ 
Jun 27, 2024 400
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2016(ኢዜአ)፦ ኢትዮ-ቴሌኮምና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ስማርት ካምፓስ ፕሮጀክት ለመተግበር የሚያስችል ሥምምነት ተፈራረሙ። ሥምምነቱን የኢትዮ-ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈፃሚ ፍሬህይወት ታምሩንና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተጠባባቂ ፕሬዚዳንት ሳሙኤል ክፍሌ (ዶ/ር) ፈርመውታል። ሥምምነቱ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የስማርት መማሪያ ክፍሎችና የተለያዩ ዘመናዊ አሰራሮችን ለማቅረብ ያስችላል ተብሏል። ሥምምነቱ የተለያዩ ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎች የተሟሉለት የትምህርት ጥራትንና አካታችነትን ለማረጋገጥ፣ የትምህርት መረጃዎችን በቀላሉ ለማግኘት፣ የቤተ-ሙከራ ፍተሻዎችን በተሻለ ተሞክሮ ለማከናወን፣ የምዘና ፈተናዎችን ለመስጠት፣ ለማረምና ውጤቶችን ወዲያውኑ ለማሳወቅ የሚያስችል ስማርት የመማሪያ ክፍሎችን (SMART CLASS ROOM) ለመገንባት ያስችላል ተብሏል። የስድስት ኪሎ ካምፓስ ግቢ የመግቢያ በሮች፣ ዋና ዋና የአስተዳደር ህንጻዎችን፣ ሙዚየም፣ ካፊቴሪያዎች፣ የቤተ-መጽሐፍት፣ የተማሪዎችና የውጪ ሀገር ዜጎች የመኖሪያ ህንጻ ሰላማዊ እንቅስቃሴና ደህንነት ለመከታተል የሚያስችል የሲሲቲቪ ካሜራ፣ የመቆጣጠሪያ ማዕከልና የካምፓስ ፋይበር ኔትወርክ ዝርጋታና ተዛማጅ የመሰረተ ልማት ግንባታ የሚያካትት ነውም ተብሏል። ሥምምነቱ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ህክምና ፋኩሊቲ የጥቁር አንበሳ አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የህክምና አገልግሎት ክፍያዎችን በቴሌብር ለመፈጸም የሚያስችል ስትራቴጂያዊ የአጋርነት ሥምምነት መሆኑን ተጠቅሷል።            
የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር እና የኢትዮጵያ ስኳር ኢንዱስትሪ ግሩፕ በትብብር ለመስራት ተስማሙ
Jun 26, 2024 338
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2016(ኢዜአ)፦ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር(ኢመደአ) እና የኢትዮጵያ ስኳር ኢንዱስትሪ ግሩፕ በጋራ በሚሰሩባቸው ጉዳዮች ላይ የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረሙ። በስምምነቱ ወቅት የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ዳንኤል ጉታ እንደገለጹት ተቋማቸው የኢትዮጵያ ስኳር ኢንዱስትሪ ግሩፕ የሀገራችንን የስኳር ፍላጎት ከማሟላት ባሻገር ለውጭ ገበያ ለማቅረብ በሚያደርጋቸው ጥረቶች ሁሉ አስፈላጊውን እገዛ ያደርጋል። በዚህም የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በራሱ አቅም ባለማቸው ቴክኖሎጂዎች እና የሰው ሀይሉን በማሰልጠን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑንም ጠቁመዋል። የኢትዮጵያ ስኳር ኢንዱስትሪ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ዋዮ ሮባ በበኩላቸው አሁን ላይ በሀገር አቀፍ ደረጃ ያለውን የስኳር ፍላጎት ለመሽፈን በተለምዷዊው አካሄድ መሄድ አዋጭ አለመሆኑን በመረዳት ተቋማቸው ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን ወደ መጠቀም መምጣቱን ገልጸዋል። ለዚህም እንደ ኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በመሳሰሉ በዘርፉ የካበተ ልምድ ካላቸዉ ተቋማት ጋር በትብብር መስራት ወሳኝ መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ ስኳር ኢንዱስትሪ ግሩፕ ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች ከመግባቢያ ስምምነቱ ባሻገር የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ምርትና አገልግሎቶችን እንዲሁም የኢትዮ ሳይበር ታለንት ማዕከልን መጎብኘታቸውን ከኢመአድ ማህበራዊ ትስስር የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት የግሉ ዘርፍ የመሪነት ሚናውን እንዲወጣ የሚያግዝ ፎረም ሊመሠረት ነው 
Jun 26, 2024 227
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2016(ኢዜአ)፦በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት የግሉ ዘርፍ የመሪነት ሚናውን እንዲወጣ የሚያግዝ ፎረም ሊመሠረት መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር አስታወቀ። ሚኒስቴሩ ከግሉ ዘርፍና ከባለድርሻ አካላት ጋር በ2016 በጀት ዓመት ዐብይ ክንውኖችና በ2017 ዓ.ም. አቅጣጫ እንዲሁም በፎረሙ ምስረታ ዙሪያ የምክክር መድረክ አካሂዷል። የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትሩ በለጠ ሞላ (ዶ/ር) እንዳሉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት ለማሳደግ መንግሥት ከግሉ ዘርፍ ጋር በመተባበርና በቁርጠኝነት እየሠራ ይገኛል። በዘንድሮ ዓመት በተካሄዱ የተለያዩ ውጤታማ ሁነቶች በአገሪቱ በቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን መስክ የተሰማራው የግሉ ዘርፍ ያለውን እምቅ አቅም ለመገንዘብ ተችሏል ብለዋል። ይህን አቅም በሚገባ አሟጦ ለመጠቀም የግልና የመንግሥት አጋርነት ፎረም ለመመስረት ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል።   የሚመሠረተው ፎረምም የግሉ ዘርፍ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ልማት የመሪነት ሚናውን እንዲወጣ የሚያግዝ ይሆናልም ሲሉ አክለዋል። በተለይም በመንግሥትና በግሉ ሴክተር መካከል ጠንካራ ትስስር በመፍጠር ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን በኢትዮጵያ እውን ለማድረግ የተለያዩ ተግባራት መከናወናቸውን ተናግረዋል። በቀጣይም የግል እና የመንግሥት አጋርነት ውጤታማ እንዲሆን መደበኛ ቅርጽ እና የአሠራር ሥርዓት ሊበጅለት እንደሚገባ ጠቁመዋል። ዘርፉን ለማሳደግ ካለው የመንግሥት ፍላጎት አንጻር በዘርፉ የተሰማሩ የግልና የመንግሥት አስፈጻሚ አካላት በመደበኛ ሁኔታ ቀርበው የሚወያዩበት የራሱ አሠራር ያለው መድረክ ለማጠናከር ዝግጅት መደረጉን ገልፀዋል። ይህም የዲጂታል ትራንስፎርሜሽንን እውን ለማድረግ በሚያስችል በአስተማማኝ ሁኔታ መሠረት ለመጣል ዕድል የመፍጠር ዓላማ ያለው መሆኑን ጠቁመዋል። የአጋርነት ፎረሙም መንግሥት፣ የግሉ ዘርፍ ተቋማት፣ ማኅበራት፣ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማትና የልማት አጋሮችን በማቀራረብና በቅንጅት የሚሰሩበት መድረክ በአስተማማኝ ሁኔታ እንዲፈጠር የሚያግዝ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ በውይይት መድረኩ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዘርፍ የተሰማሩ ማኅበራት፣ የግል እና የመንግሥት ተቋማት አመራሮችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።
የጀርመን የልማት ተራድኦ ድርጅት (ጂ አይ ዜድ) ለቴክኒክና ሙያ ሥልጠና ዘርፍ የሚያደርገውን ድጋፍ አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጸ  
Jun 22, 2024 458
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 15/2016 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና ዘርፍ ብቁና ተወዳዳሪ የሰው ኃይል ለማፍራት ለምታከናውነው ተግባር የጀርመን የልማት ተራድኦ ድርጅት (ጂ አይ ዜድ) ሙያዊ ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገለጸ። ኢትዮጵያ በፈጠራ ክህሎት የታነጸ አምራች የሰው ኃይል በማፍራት ዘላቂ ልማትን ለማረጋገጥ በትምህርት ዘርፍ የፖሊሲና ስትራቴጂ ማሻሻያዎችን በማድረግ እየተገበረች ትገኛለች። ከእነዚህ መካከል በተግባር የተደገፈ አዳዲስ የፈጠራ ውጤቶችን በማፍለቅ አምራች ኢንዱስትሪውን ለመደገፍ ትልቅ ሚና ያላቸው የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና ተቋማት ተጠቃሽ ናቸው። የጂ አይ ዜድ የዘላቂ ትምህርትና ሥልጠና መርኃ-ግብር ኃላፊ ሞሃመድ አሊ ካን (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደተናገሩት፤ ኢትዮጵያ ብቁና ተወዳዳሪ የሰው ኃይል ለማፍራት እያከናወነች ላለው ተግባር በትብብር እየተሰራ ነው። በቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና ተቋማት በፈጠራና ክህሎት ብቃት ያለው የሰው ኃይል ለማፍራት ተግባራዊ እየተደረገ ላለው ፖሊሲ የቴክኒክና የሥልጠና ዘርፍ የሙያ ድጋፍ በማድረግ እየሰሩ መሆኑን ገልፀዋል። አሁን ላይ ደግሞ በዘርፉ ተቋማት ዲጂታላይዜሽን ሥራዎችን እያገዙ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህ ድጋፍ በቀጣይም ይበልጥ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ነው ያረጋገጡት። በሚኒስትሮች ምክር ቤት የጸደቀው አዲሱ የትምህርትና ሥልጠና ፖሊሲ የትምህርትና የሥልጠና ዘርፉን በደንብ አሰናስሎ ከማስኬድ አኳያ የነበሩ ክፍተቶችን የሚሞላና ከታችኛው የትምህርት እርከን ጀምሮ በሙያ የተቃኘ እንዲሆን ያስችላል ተብሏል። ፖሊሲው ከሙያ ሥልጠና አኳያ ከአስተሳሰብ ጀምሮ ያሉ ዝንፈቶችን የሚያስተካክልና የሥልጠና ጥራት፣ አግባብነት፣ ተደራሽነትና ፍትሃዊነትን የሚያስተናግድ ሥርዓት የሚዘረጋ መሆኑም ተጠቁሟል። ኃላፊውም ይህንን በመደገፍ፤ አዲሱ ፖሊሲ ለቴክኖሎጂ፣ ፈጠራ፣ የግሉን ዘርፍ ለማሳተፍ፣ ለጥራት እንዲሁም ለሥርዓተ-ፆታ እኩልነት የሰጠው ትኩረት የሚበረታታ መሆኑን ጠቅሰዋል። ፖሊሲው በአግባቡ ከተተገበረ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠና ሥርዓትን በማሻሻል በዘርፉ ትልቅ ለውጥ ያመጣል የሚል እምነት እንዳላቸውም ገልፀዋል። የግሉ ዘርፍ ከሥልጠና ተቋማት ጋር ተቀራርቦ በመሥራት በተግባር የተደገፈ ክህሎትና እውቀት ያለው የሰው ኃይል ለማፍራት የተሰጠው ትኩረት የሚበረታታ እንደሆነ ጠቁመዋል። የኢትዮጵያን ምጣኔ ኃብት የሚያሳልጡ በፈጠራ ክህሎት የታነጹ ሙያተኞችን ለማፍራት መንግሥት የሚያከናውናቸውን ተግባራት ለማሳካት በትብብር መሥራታቸውን እንደሚቀጥሉም ኃላፊው አረጋግጠዋል።    
በ13 የመንግስት ተቋማት የኢ-ፍሊት ማኔጅመንት የሙከራ ትግበራ ተጀመረ
Jun 20, 2024 511
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 13/2016(ኢዜአ)፦በተሽከርካሪ ሥምሪትና አጠቃቀም የሚባክነውን ሃብት ለመቆጣጠር የሚያስችል የኢ-ፍሊት ማኔጅመንት በ13 የመንግስት ተቋማት የሙከራ ትግበራ ተጀመረ። የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን የኢ-ፍሊት ማኔጅመንት (e-Fleet Management) የሙከራ ትግበራ ከሚደረግባቸው 13 የፌዴራል መንግስት ተቋማት ጋር ውይይት አድርጓል። ኢ-ፍሊት ማኔጅመንት ማለት ክንውኖችን በጥራት፣ በብቃት፣ በሰዓት እና በበጀት መጥኖ መፈፀም የሚያስችል ዘመናዊ የአሰራር ስርአት ነው። በተለይም የተሽከርካሪ ንብረት አጠቃቀም፣ አያያዝ፣ የግዥ ሂደትና አወጋገድን በተመለከተ የላቀ ጠቀሜታ ያለው የአሰራርና ቁጥጥር ስርአት መሆኑ ይነገርለታል። በመሆኑም የመንግስት ግዥና ንብረት ባለስልጣን በተሽከርካሪ ሥምሪትና አጠቃቀም የሚባክነውን ሃብት ለመቆጣጠር በ13 የመንግስት ተቋማት የኢ-ፍሊት ማኔጅመንት የሙከራ ትግበራ ጀምሯል። የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ሃጂ ኢብሳ፤ በመንግስት ተቋማት በግዥና ንብረት የሚስተዋለውን ሙስና እና ብልሹ አሰራር ለመከላከል የሚያስችሉ አሰራሮች በመተግበር ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል። ለዚህም ሲባል የዲጂታል ስርዓት በስፋት ተግባራዊ እየተደረገ ሲሆን በ160 የመንግስት ተቋማት የኤሌክትሮኒክ ግዥ ተግባራዊ መደረጉን ለአብነት ጠቅሰዋል። በተመሳሳይ በተሽከርካሪ ሥምሪትና አጠቃቀም የሚባክነውን ሃብት ለመቆጣጠር የሚያስችል የኢ-ፍሊት ማኔጅመንት በ13 የመንግስት ተቋማት የሙከራ ትግበራ ተጀምሯል ብለዋል በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የለማው የኢ-ፍሊት ማኔጅመት መተግበሪያ የተሽከርካሪ ሥምሪትና አጠቃቀምን ከማሻሻል ባለፈ የሃብት ብክነትን የሚያስቀር መሆኑን ገልጸዋል። አዲሱ መተግበሪያ ተሸከርካሪው ያለበትን ቦታ የማመላከት፣ ከተሽከርካሪ ጥገና እና ነዳጅ ጋር የተያያዙ ወጪዎችን መከታተል የሚያስችል መሆኑንም አስረድተዋል። በመሆኑም በሙከራ ደረጃ የተጀመረው ኢ-ፍሊት በቀጣይ በሁሉም የመንግሥት ተቋማት ተግባራዊ ይደረጋል ብለዋል። የሙከራ ትግበራ ከሚደረግባቸው ተቋማት መካከል የገንዘብ ሚኒስቴር እና የግብርና ሚኒስቴር የሚጠቀሱ ሲሆን የየዘርፉ ሃላፊዎች የዲጅታል አሰራሩ ይስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን ሊፈታ እንደሚችል ያላቸውን እምነት ገልጸዋል።   የገንዘብ ሚኒስቴር የስራ አመራር ስራ አስፈፃሚ ግዛው ኃይሉ፤ ኢ-ፍሊት ከተሽከርካሪ ጥገና እና ነዳጅ ጋር የተያያዙ ችግሮችን ለመፍታት ሁነኛ መፍትሄ መሆኑን ጠቅሰዋል።   በግብርና ሚኒስቴር የመሰረታዊ አገልግሎት ስራ አስፈፃሚ ግዛቸው አሰግድ በበኩላቸው፤ ለግልጽ አሰራርና የሃብት ክትትል መተግበሪያው አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል። ለአሰራሩ ውጤታማነትም አስፈላጊውን ሁሉ እገዛና ትብብር ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸውን ስራ አስፈፃሚዎቹ አረጋግጠዋል።
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም