በክረምት ወራት የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በመውሰድ የቴክኖሎጂ አቅም እና ተወዳዳሪነታችንን ለማሳደግ እንሰራለን- ተማሪዎች

ዲላ፤ ሰኔ 26/2017 (ኢዜአ)፦በክረምት ወራት ተጨማሪ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በመውሰድ የቴክኖሎጂ አቅምና ተወዳዳሪነታቸውን ለማሳደግ እንደሚሰሩ በጌዴኦ ዞን የሚገኙ ተማሪዎች ገለጹ።

በዞኑ በክረምት ወራት ከ3 ሺህ ለሚበልጡ ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለመስጠት ዝግጅት መደረጉም ተመላክቷል።

አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ ተማሪዎች መካከል የዲላ ዶንቦስኮ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ቅድስት ወርቅአየሁ ቀደም ሲል በፕሮግራም ፋንዳሜንታል ዘርፍ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስዳ የምስክር ወረቀት ማግኘቷን ገልጻለች።

ይህም በሶፍት ዌር ግንባታ አቅም እንደፈጠረላት ገልጻ በክረምት ወራትም በሌሎች የኢትዮ ኮደርስ ዲጂታል ስልጠና ዘርፎች የሚሰጠውን ስልጠና በመከታተል ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግ መዘጋጀቷን ገልጻለች።


 

በሕጻናት ጌምና ጨዋታ በአፍሪካ ኮደረስ ቻሌንጅ ውድድር የፈጠራ ሥራዋን በማቅረብ ተሸላሚ መሆኗን ያነሳችው ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ ተማሪ ከነአን አንትንብዬ ናት።

ከዚህ ቀደም የወሰደችው የኮደርስ ስልጠና የፈጠራ አቅሟን እንዳሳደገላት ጠቁማ፣ በክረምት ወራት ስልጠናውን በማጠናከር ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን ለማሳደግ መዘጋጀቷን ተናግራለች።


 

በዲላ ከተማ የሚገኘው ቆፌ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪ ቤዛኩሉ ገዛኸኝ በበኩሉ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና በቀለም ትምህርት ያለውን ውስን እውቀት በማስፋት ተግባራዊ እውቀት እንዲጨብጥ ያደረገው መሆኑን ተናግሯል።

ስልጠናው ለቴክኖሎጂ ያለውን ቅርበት እንዳሳደገለት ገልጾ፣ በዲጂታል ዓለም ብቁ ሆኖ ለመገኘትና ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ   የስልጠናው ፋይዳ የጎላ መሆኑን ተናግሯል።


 

የክረምት ወራት የእረፍት ጊዜውን  በኢትዮ ኮደርስ ተጨማሪ ስልጠና በመውሰድ አቅሙን ለማሳደግ ማቀዱንም ገልጿል። 

በትምህርት ቤቱ ከ150 በላይ ተማሪዎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ወስደው የምስክር ወረቀት ማግኘታቸውን የገለጹት ደግሞ የዲላ ዶንቦስኮ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት መምህር አንዱአለም ፀጋዬ ናቸው።


 

ስልጠናውን የወሰዱ ተማሪዎች የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ የአስተሳሰብ አድማሳቸውን እንዲያሰፉ ከማድረግ ባለፈ  ችግር ፈቺ የፈጠራ ሥራዎችን የማበልጸግ ሥራ መጀመራቸውን ተናግረዋል። 

በተያዘው ክረምት ወራትም በትምህርት ቤቱ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናን አጠናክሮ ለማስቀጠል ዝግጅት መደረጉን ጠቁመዋል።

የጌዴኦ ዞን ሳይንስ፣ ኢንፎርሜንሽንና ቴክኖሎጂ መምሪያ ሃላፊ አቶ ደረጀ ሾንጣ በበኩላቸው እንዳሉት በክረምት ወራት በዞኑ ከ3 ሺህ ለሚልቁ ዜጎች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ለመስጠት ዝግጅት ተደርጓል።


 

ለዚህም በከፍተኛ እና በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የስልጠና ማዕከላትን የማጠናከርና የኔትወርክ ዝርጋታ ሥራዎች መጠናቀቃቸውን ገልጸዋል።

በበጀት ዓመቱ በዞኑ 9 ሺህ 714 ዜጎችን በኢትዮ ኮደርስ ለማሰልጠን ታቅዶ ወደስራ መገባቱንም አቶ ደረጀ አስታውሰዋል።

እስካሁንም ስልጠናውን ለመውሰድ ከ8ሺህ በላይ ዜጎች እንደተመዘገቡ ጠቁመው፣ ከእነዚህ ውስጥ 3ሺህ 400 ዎቹ ስልጠናቸውን አጠናቀው የምስክር ወረቀት አግኝተዋል ብለዋል። 

በአሁኑ ወቅትም ስልጠናውን እየተከታተሉ ያሉ ዜጎች አሉ ያሉት አቶ ደረጀ፣ በክረምትም ስልጠናውን አጠናክሮ በማስቀጠል ከዕቅድ በላይ ለማስመዝገብ እንደሚሰራ ተናግረዋል።

የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና የዜጎችን የቴክኖሎጂ እውቀት በማጎልበት የፈጠራ አቅማቸውንና ተወዳዳሪነታቸውን እያሳደገው መሆኑን  ጠቅሰው፣  የስልጠናው ተሳታፊዎችም ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል።

 

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም