ኢትዮጵያ በአስደናቂ የለውጥ ጎዳና ላይ ትገኛለች- የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀመድ አሊ የሱፍ - ኢዜአ አማርኛ
ኢትዮጵያ በአስደናቂ የለውጥ ጎዳና ላይ ትገኛለች- የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀመድ አሊ የሱፍ

አዲስ አበባ፤ ሰኔ 30 /2017 (ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በብዝሃ የኢኮኖሚ ዘርፍ በአስደናቂ የለውጥ ጎዳና ላይ ትገኛለች ሲሉ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀመድ አሊ የሱፍ ገለጹ።
ኢትዮጵያ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሳል አመራር በአስደናቂ የለውጥ ጎዳና ላይ እንደምትገኝም ተናግረዋል።
3ኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም መካሄድ ጀምሯል።
በፎረሙ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል፣ የአፍሪካ ሀገራት ሚኒስትሮች፣ የፈጠራ ባለሙያዎች፣ ሥራ ፈጣሪዎች፣ የዘርፉ ምሁራን እና ባለድርሻ አካላት ታድመዋል።
የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር መሀመድ አሊ የሱፍ፥ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት እንድታስመዘግብ እየሰጡ ላለው ድንቅ አመራርም አድናቆታቸውን ገልጸዋል።
በአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራን እና የኢኮኖሚ ለውጥን ማሳካት የልማት ዋነኛ መሠረት ነው ብለዋል።
ወጣቶችና ሴቶች የዲጂታል ክህሎት ስልጠና እና የፋይናንስ ድጋፍ እንዲያገኙ ማድረግም ይገባል ነው ያሉት።
በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ አስደናቂ ስኬት እያስመዘገበች መሆኗን ገልጸዋል።
አዲስ አበባን ጨምሮ በርካታ የኢትዮጵያ ከተሞች በአስደናቂ እና ህይወት ቀያሪ የዕድገት ጉዞ ላይ መሆናቸውን ገልጸው፥ ይህም የድንቅ አመራር ውጤት ማሳያ ነው ብለዋል።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) አመራር ኢትዮጵያ በግብርናው መስክም በስንዴና ሌሎች የሰብል ምርቶች ራስን ከመቻል አልፋ ኤክስፖርት እስከማድረግ ደርሳለች ነው ያሉት።
ከአፍሪካ ህዝብ ከ60 በመቶ በላይ የሚሆነው ከ25 ዓመት በታች ዕድሜ ላይ የሚገኝ ወጣት ኃይል መሆኑን በማውሳት፥ በየዓመቱ የሚፈጠረው የሥራ ዕድል አሁንም አነስተኛ ነው ብለዋል።
አፍሪካ በዓለም የምርት እሴት ሰንሰለት ውስጥ ያላት ድርሻም ከሦስት በመቶ በታች መሆኑን በማንሳት ይህን ከፍ ማድረግ እንደሚገባ አፅንኦት ሰጥተዋል።
ግብርና በአፍሪካ ከፍተኛ የሥራ ዕድል መፍጠሪያ መስክ መሆኑን ጠቅሰው፥ ከ60 በመቶ በላይ ህዝብ ህይወቱን የሚመራበትም ነው ብለዋል።
የአፍሪካ ነፃ ንግድ ቀጣናም ለሥራ ዕድል ፈጠራ ተጨማሪ አቅም እንደሆነ በማንሳት፥ ወደ ተግባር ማስገባት አለብን ብለዋል።
የግሉ ዘርፍ፣ አነስተኛና ከፍተኛ ድርጅቶች በነፃ የንግድ ቀጣናው በመሳተፍ ተጠቃሚ ለመሆን እንዲዘጋጁም ጥሪ አቅርበዋል።
ቴክኖሎጂን በማስፋፋት አዳዲስ ሥራዎችን የመፍጠርን አስፈላጊነት በማንሳት፥ የወጣቶች ፈጠራን በማበረታታት ፈተናዎችን የሚቋቋም ዲጂታል ሥርዓትን እንዲገነቡ ማድረግ እንደሚገባ ጠቅሰዋል።
በሁሉም መስክ አካታች ልማትን እውን በማድረግ ድህነትን ከአፍሪካ የማጥፋት ግብን ለማሳካት የጋራ ሥራ ወሳኝ መሆንም ገልጸዋል።