ኢትዮጵያ ለበርካታ ዜጎች የሥራ እድል የፈጠሩ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን እየተገበረች ነው

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ አዲስ አበባን ጨምሮ በሁሉም አካባቢ እያከናወነቻቸው ያሉ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች ለበርካታ ዜጎች የሥራ እድል  እየፈጠሩ መሆኑን መገንዘባቸውን የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም ተሳታፊዎች ገለጹ።

በአዲስ አበባ እየተካሄደ በሚገኘው ሦስተኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም በአህጉሪቱ ያለውን እምቅ አቅም በመጠቀም ለአፍሪካውያን ወጣቶች የሥራ እድል ለመፍጠር ትብብርን የሚያጎለብት እንደሆነ ተሳታፊዎች ገልጸዋል።

ኡጋንዳዊው ተሳታፊ ናምጎ ጆብ እንደገለጸው፤ ፎረሙ በአፍሪካ ያለውን እምቅ አቅም በመጠቀም በሥራ እድል ፈጠራ የተያዙ እቅዶችን በትብብር መተግበር ለአህጉሪቷ ወጣቶች ተስፋ የሚሰጥ ነው።

ይህም አፍሪካውያን ወጣቶች በአገራቸው ሰርተው የመበልጸግ ርዕያቸውን እውን በማድረግ ከስደት እንደሚታደጋቸው ገልጿል። 

ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ አዲስ አበባ የመጣው እ.ኤ.አ በ2023 እንደነበር በማስታወስ፤ አሁን ለሁለተኛ ጊዜ ሲመጣ የአዲስ አበባ የመሰረተ ልማት መስፋፋትና የከተማዋ እድገት እንዳስገረመውም ጠቅሷል።

የአዲስ አበባ ዘመናዊ መሰረተ ልማት፣ የከተማ ውበት፣ የጎዳናዎች ስፋትና ጽዳት "በአፍሪካ የአውሮፓ ከተማ ውስጥ እንዳለሁ ተሰምቶኛል" ሲል የከተማዋን ዕድገት አድንቋል።

በከተማዋ እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች ለበርካታ ዜጎች የስራ እድል የሚፈጥሩ መሆኑን መገንዘቡን  በማንሳት፥ ኢትዮጵያ በብሩህ ተስፋ ጉዞ ላይ ናት ብለዋል።

በኮሜሳ የሴት ነጋዴዎች ማህበር ፌዴሬሽን የቦርድ ሊቀ መንበር ሞሪን ሶቦይ ወደ ኢትዮጵያ በሚመጡበት ወቅት የሚያገኙት አዳዲስ ለውጥ ሀገሪቱ በፈጣን እድገት ላይ መሆኗን የሚያመላክት እንደሆነ ገልጸዋል።


 

ሌሎች የአፍሪካ አገራትም ከኢትዮጵያ የዕድገት ጉዞ ልምድ ሊወስዱ እንደሚገባ ጠቁመዋል።

አዲስ አበባ በከተማ ውበት፣ እድገትና ጽዱ አካባቢን በመፍጠር እያሳየች ያለው ለውጥም ለመኖሪያ ምቹ ያደርጋታል ነው ያሉት።

በኢትዮጵያ የዓለም አቀፉ የስራ ድርጅት ዋና የቴክኒክ አማካሪ አንቶኒ አይንታ ኢትዮጵያ ለራሷ ብቻ ሳይሆን ለጎረቤት አገሮችም አቅም መሆን የሚችል ብቁ የሰው ሃይል አላት ብለዋል። 


 

አህጉሪቱን በንግድና አገልግሎት ለማስተሳሰር ከተያዘው ራዕይ ጎን ለጎን በሰለጠነ የሰው ሃይል የወጣቶችን እውቀት በመጠቀም በስራ ፈጠራ ማስተሳሰር እንደሚቻል ጨምረዋል።

ሦስተኛው የአፍሪካ የሥራ ዕድል ፈጠራ ፎረም የግብርና እሴት ሰንሰለት፣ ዲጂታላይዜሽንና የፋይናንስ አካታችነትን በማረጋገጥ አስተማማኝ የሥራ ዕድል ለመፍጠር ቀጣናዊ ትስስርን ማጠናከር ላይ ምክክር በማድረግ ዛሬም ቀጥሎ ተካሂዷል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም