የቱሪዝም ዘርፉን ተወዳዳሪ ለማድረግ ፈጠራ የተሞላበት የቴክኖሎጂ ውጤቶችን መጠቀም ይገባል -የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ

አዲስ አበባ፤ ሐምሌ 1/2017(ኢዜአ)፦ የቱሪዝም ዘርፉን ተወዳዳሪ ለማድረግ ፈጠራ የተሞላበት የቴክኖሎጂ ውጤቶች መጠቀም እንደሚገባ የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ ገለፁ። 

ቱሪዝም ሚኒስቴር ከኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በሀገራችን የሚገኙ መዳረሻዎችን እና የቱሪዝም አገልግሎቶችን በተሻለ ሁኔታ በማስተዋወቅ “ቪዚት ኢትዮጵያ" የተሰኘ ሀገር በቀል የግብይት ድረገፅ በይፋ ስራ ጀምሯል። 

ቪዚት ኢትዮጵያ የቱሪዝም ዕምቅ ሀብት፣ የቱሪዝም መዳረሻዎች ለአለም የሚያስተዋውቅ ድረገፅ መሆኑ ተገልጿል። 


 

በይፋ ማድረጊያ መርሃግብሩ ላይ የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ፣ የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግሥት ሀሚድ፣ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ተስፋሁን ጎበዛይና ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት ኃላፊዎችና ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል። 

የቪዚት ኢትዮጵያ የቱሪዝም መዳረሻዎችንና አገልግሎት ሰጪዎችን የሚያስተዋውቅ እንዲሁም ቻት ቦትን ያካተተ ነው ተብሏል። 


 

በዚህ ወቅት የቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ እንዳሉት ኢትዮጵያ በርካታ የቱሪዝም ፀጋዎች አሏት። 

የቱሪዝም ዘርፉን ተወዳዳሪ ለማድረግ ፈጠራ የተሞላበት የቴክኖሎጂ ውጤቶች መጠቀም ይገባል ብለዋል። 

ቪዚት ኢትዮጵያ የቱሪዝም መዳረሻዎችን የተመለከተ ወቅታዊና ጥራቱን የጠበቀ መረጃ ማቅረብ የሚያስችል መሆኑንም ተናግረዋል። 

የቱሪዝም ዘርፍ ተዋንያንን በአንድ በይነ መረብ የሚያስተሳስር ነው ብለዋል። 

የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ዋና ዳይሬክተር ትዕግሥት ሀሚድ በበኩላቸው ኢትዮጵያ የበለፀገ የባህል ስብጥርና የቱሪዝም ሀብት ያላት አገር መሆኗንም ገልጸዋል። 


 

ያለንበት የዲጂታል ዘመን ጎብኚዎች ባሉበት በመሆን ቪዚት ኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፉን አለም አቀፍ ተወዳዳሪነት የሚያሳድጉበት ነው ብለዋል። 

ቪዚት ኢትዮጵያ ደህንነቱ የተጠበቀና ተጠቃሚን ማዕከል ያደረገ መሆኑንም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም