ማዕከሉ በምርምር ያገኛቸውን አምስት የሰብልና የጥራጥሬ ዝርያዎችን ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ ለቋል

ሮቤ፤ ሐምሌ 1/2017 (ኢዜአ)፡- የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል በምርምር ያገኛቸውን አምስት የሰብልና የጥራጥሬ ዝርያዎች ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ  መልቀቁን አስታወቀ። 

በምርምር የተገኙ ዝርያዎች አርሶ አደሩ በምግብ ራስን ለመቻል የሚያደርገውን ጥረት የሚያግዙና ተጨማሪ ገቢን በማስገኘት ረገድ የጎላ አስተዋጽኦ ያላቸው መሆኑ ተመልክቷል።


 

የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል ዳይሬክተር አቶ ታመና ሚደቅሳ እንዳመለከቱት፤ ማዕከሉ የአርሶ አደሩን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ የሚደረገውን ጥረት በምርምር እየደገፈ ነው።

ማዕከሉ ባለፉት ዓመታት በምርምር ያፈለቃቸውና በሄክታር እስከ 70 ኩንታል  ምርት የሚሰጡ " ቦኩ፣ ሳነቴና ሃጫሉ"  የተሰኙ  የስንዴ ዝርያዎችን ለተጠቃሚው ማድረሱን አውስተዋል።  


 

በምርምር የወጡ የተሻሻሉ ዝርያዎች በማዕከሉ ማሳ ፣ በኦሮሚያ ምርጥ ዘር ኢንተርፕራይዝና በአርሶ አደሩ ማሳ ላይ በስፋት ተባዝተው ለአርሶ አደሩ ተደራሽ እንዲሆኑ በትኩረት እየተሰራ መሆኑንም ገልጸዋል። 

አቶ ታመና ፤  ማዕከሉ ቀደም ሲል ጀምሮ ምርምር ሲያካሄድባቸው ቆይቶ በተጠናቀቀው የበጀት ዓመት ያወጣቸው አምስት አዳዲስ የሰብልና የጥራጥሬ ዝርያዎች ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ መልቀቁን አስታውቀዋል።  


 

በምርምር ከተለቀቁ ዝርያዎች መካከል የፓስታና ማካሮኒ ስንዴ፣ባቄላ፣ምስርና ሁለት የተልባ ዝርያዎች እንደሚገኙበት ጠቅሰዋል።

በብሔራዊ የዝርያ አፅዳቂ ኮሚቴ ይሁንታ ካገኙ በኋላ የተለቀቁት እነዚህ ዝርያዎች በሽታን በመቋቋም ከነባሩ  ዝርያዎች ከ15 በመቶ በላይ የምርታማነት ብልጫ ያላቸው መሆኑንም አክለዋል።


 

የሲናና ግብርና ምርምር ማዕከል በ1978 ዓ.ም የተቋቋመ ሲሆን፤ እስካሁን 116 የሚሆኑ የሰብልና የእንስሳት መኖ ላይ ያተኮሩ ዝርያዎችን በምርምር በማፍለቅ ለተጠቃሚው ማሰራጨቱን ከምርምር ማዕከሉ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም