ቀጥታ፡

ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካታች የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥ ቁልፍ ሚና ይጫወታል

አዲስ አበባ፤ ሕዳር 24/2018 (ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካታች የኢኮኖሚ ዕድገትን ይበልጥ ለማረጋገጥ ቁልፍ ሚና የሚጫወት መሆኑን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ።

የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ያዘጋጀው የ2025 'ዳይመንድ ክለብ ሲምፖዚየም'  Club Symposium) "አካታች ወደ ፊትን ለመፍጠር ዓለም አቀፍ የዲጂታል አመራር ማጠናከር" በሚል መሪ ሀሳብ እየተካሄደ ነው።

በሲምፖዚየሙ መክፈቻ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ባደረጉት ንግግር ቴክኖሎጂ የዓለምን ከባድና ወስብስብ ችግሮች ለመፍታት ዕድሎችን ይዞ መምጣቱን ተናግረዋል።

በሌላ በኩል ቴክኖሎጂን በአግባቡ አለመጠቀም አዲስ ፈተናዎችን የመፍጠር አቅም እንዳለው ጠቁመው፤

ይህን ፈተና ለመፍታት ሀገራት ትብብራቸውን የበለጠ ማጠናከር አለባቸው ብለዋል።

በቅርቡ የፀደቀው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካታች የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥና የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማጎልበት ቁልፍ ሚና እንዳለውም ነው አጽንኦት የሰጡት።

የኢትዮጵያ ዲጂታል እድገት አበረታች መሆኑን ገልጸው፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች በዲጂታል መለያ ሥርዓቶች ውስጥ እየተካተቱ መሆኑን ተናግረዋል።

የዲጂታል መሠረተ ልማቶች እየተስፋፉ እንዲሁም ኤሌክትሮኒክ የመንግስት አገልግሎቶች እያደጉ መምጣታቸውን አንስተዋል።

የመረጃ ግላዊነት፣ ሳይበር ደህንነት እና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ላይ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች በአንድ ሀገር ብቻ ሊፈቱ እንደማይችሉ አመላክተዋል።

የሰዎች መብቶች የሚጠበቅበት እና ፈጠራን ከድንበር በላይ እንዲያድግ የሚያስችል አዲስ ዓለም አቀፍ የትብብር ሞዴሎች መገንባት እንደሚገባም ጠቁመዋል።

የዛሬው ሲምፖዚየም ለመነጋገር ብቻ ሳይሆን ወደ ተግባር ለመሸጋገር የሚያስችል ጊዜ መሆን እንዳለበት ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም