ቀጥታ፡

የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት መሰረት የሆኑ ቁልፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ አስችሏል

አዲስ አበባ፤ ሕዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት መሰረት የሆኑ ቁልፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ ማስቻሉን የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉቀን ቀሬ ገለጹ።

የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች የተተከሉ ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎችን በይፋ አገልግሎት አስጀምሯል።


 

የContinious Operating Reference Station /CORS/ -ጣቢያ በቋሚነት መሬት ላይ የሚተከል የሳተላይት መረጃን ያለማቋረጥ የሚቀበልና የሚያደራጅ ቴክኖሎጂ ነው ተብሏል።

እንዲሁም የአንድን ቦታ መገኛ ከጂ ፒ ኤስ ሳተላይቶች 24 ሰዓት በመቀበል ከፍተኛ ጥራት ያለው መረጃ የሚያቀርብ እንደሆነም ተገልጿል።

የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉቀን ቀሬ  እንደገለጹት፥ የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ባለፉት አምስት ዓመታት ለዲጂታል ኢኮኖሚ ልማት መሰረት የሆኑ ቁልፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ አስችሏል።

የዲጂታል መታወቂያ ምዝገባን በማስጀመረ፣ በቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ግንባታ፣ በህግ ማእቀፎች እንዲሁም በ5 ሚሊዮን ኮደርስ ኢኒሼቲቭ በክህሎት ግንባታ ለውጥ መምጣቱን ጠቁመዋል።


 

ከሳተላይት መረጃ መቀበያ  ጀምሮ የቴክኖሎጂ መሠረተ ልማት ግንባታ ላይ ሠፋፊ ተግባራት መከናወናቸውን በማንሳት፥ በቀጣይም  ለዲጅታል መሠረተ ልማትና ለዲጅታል ኢኮኖሚ መስፋፋት በትብብር እንደሚሠራ ጠቁመዋል።

የከተማ እና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን በበኩላቸው፥ ዛሬ ሥራ የጀመሩት ጣቢያዎች በከተሞች እየተመዘገበ ያለውን እመርታዊ ለውጥ በማጠናከር ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አንስተዋል።


 

በተለይም ከተሞችን በፕላን እንዲሁም በከተሞች ያለ መሬትን ቆጥሮ መዝግቦ በፍትሀዊነት ለመምራት እና የቅየሳን ትክክለኛነትን ለማረጋገጥ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖራቸው ጠቅሰዋል።

ከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር በቀጣይም 14 ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎች (Continious Operating Reference Station /CORS/ ለመገንባት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ (ዶ/ር)፥ ዛሬ ሥራ የጀመሩት መረጃ ተቀባይ ጣቢያዎች ለቅየሳ ሙያተኞች፣ ለተመራማሪዎች፣ ለአደጋ ስጋት ተንታኞች፣ ለመልክዓ ምድር እና ለልዩ አገልግሎት ካርታ አዘጋጅ ባለሙያዎች የቦታዎችን አሁናዊ ሁኔታ መረጃ ለማግኘት እንደሚያስችሉ ገልጸዋል።


 

የህንጻ፣ የመንገድ፣ የድልድይ እና ግድብ ግንባታ ፕሮጀክቶች ጥራት ባለው ጂኦስፓሻል መረጃ ላይ ተመስርተው እንዲነደፉና እንዲገነቡ  ከፍተኛ ፋይዳ እንዳላቸው ጠቁመዋል።

የግብርና፣ የኢንዱስትሪ፣ የማዕድንና ሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች እንዲዘምኑ በቂ መረጃ በማቅረብ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖራቸውም ነው ያነሱት።

በተጨማሪም የመሬት አስተዳደር ዘመናዊ እና ጥራት ያለው እንዲሆን ያስችላሉ ብለዋል።

ኢንስቲትዩቱ ጣቢያዎቹን ለቅየሳ ስራዎች እና ለካርታ ዝግጅት እንዲሁም ምርምር ለመስራት በሰፊው እንደሚጠቀምባቸው አንስተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም