ቀጥታ፡

የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎችን አገልግሎት አስጀመረ

አዲስ አበባ፤ ህዳር 22/2018(ኢዜአ)፦የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች የተተከሉ ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎችን በይፋ አገልግሎት አስጀምሯል።

የከተማ እና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ፈንታ ደጀን በዚሁ ወቅት፥ ዛሬ ሥራ የጀመሩት ጣቢያዎች በከተሞች እየተመዘገበ ያለውን እመርታዊ ለውጥ በማጠናከር ረገድ ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳላቸው አንስተዋል።


 

በተለይም ከተሞችን በፕላን እንዲሁም በከተሞች ያለ መሬትን ቆጥሮ መዝግቦ በፍትሀዊነት ለመምራት እና የቅየሳን ትክክለኛነትን ለማረጋገጥ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖራቸው ጠቁመዋል።

በመረጃ ላይ የተመሰረተ ውሳኔ አሰጣጥን በማዳበር እና ተጠቃሚዎች በቀላሉ ፈጣን አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላሉ ነው ያሉት።

የከተማና መሠረተ ልማት ሚኒስቴር በቀጣይም 14 ከሳተላይት ያለማቋረጥ መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎች (Continious Operating Reference Station /CORS/ ለመገንባት እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል። 

የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሙሉቀን ቀሬ በበኩላቸው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2025 ስትራቴጂ ለዲጂታል ልማት መሰረት የሆኑ ቁልፍ ስኬቶች እንዲመዘገቡ ማስቻሉን ጠቁመዋል።


 

የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ግንባታ ላይ ሠፋፊ ተግባራት መከናወናቸውን በማንሳት፥ በቀጣይም ሚኒስቴሩ ከሳተላይት መረጃ የሚቀበሉ ጣቢያዎችን ለማስፋፋት በትብብር እንደሚሠራ ጠቁመዋል።

የስፔስ ሳይንስ እና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር አብዲሳ ይልማ (ዶ/ር)፥ ዛሬ ሥራ የጀመሩት መረጃ ተቀባይ ጣቢያዎች ዘመናዊ ቴክኖሎጂ የተሟላላቸው ናቸው ብለዋል።

ለቅየሳ ሙያተኞች፣ ለተመራማሪዎች፣ ለአደጋ ስጋት ተንታኞች፣ ለመልክዓ ምድር እና ለልዩ አገልግሎት ካርታ አዘጋጅ ባለሙያዎች የቦታዎችን አሁናዊ ሁኔታ መረጃ ለማግኘት እንደሚያስችሉ ገልጸዋል።


 

የህንጻ፣ የመንገድ፣ የድልድይ እና ግድብ ግንባታ ፕሮጀክቶች ጥራት ባለው ጂኦስፓሻል መረጃ ላይ ተመስርተው እንዲነደፉና እንዲገነቡ  ከፍተኛ ፋይዳ እንዳላቸው ጠቁመዋል።

የግብርና፣ የኢንዱስትሪ፣ የማዕድንና ሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች እንዲዘምኑ በቂ መረጃ በማቅረብ የላቀ ፋይዳ እንደሚኖራቸውም ነው ያነሱት።

በተጨማሪም የመሬት አስተዳደርን ዘመናዊ እና ጥራት ያለው እንዲሆን ያስችላሉ ብለዋል።

ኢንስቲቲዩቱ ይህን ጣቢያዎቹን ለቅየሳ ስራዎች እና ለካርታ ዝግጅት እንዲሁም ምርምር ለመስራት በሰፊው እንደሚጠቀምባቸው አንስተዋል።

የContinious Operating Reference Station /CORS/ -ጣቢያ በቋሚነት መሬት ላይ የሚተከል የሳተላይት መረጃን ያለማቋረጥ የሚቀበልና የሚያደራጅ ቴክኖሎጂ ነው ተብሏል።

እንዲሁም የአንድን ቦታ መገኛ ከጂ ፒ ኤስ ሳተላይቶች 24 ሰዓት በመቀበል ከፍተኛ ጥራት ያለው መረጃ የሚያቀርብ እንደሆነም ተገልጿል።

 

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም