በዲጂታል ዘመን የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመከላከልና መፍትሄ ለመስጠት አዲስና ዓለም አቀፋዊ የትብብር ሞዴል መገንባት ያስፈልጋል - ኢዜአ አማርኛ
በዲጂታል ዘመን የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመከላከልና መፍትሄ ለመስጠት አዲስና ዓለም አቀፋዊ የትብብር ሞዴል መገንባት ያስፈልጋል
አዲስ አበባ፤ ሕዳር 24/2018(ኢዜአ)፦ በዲጂታል ዘመን የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመከላከልና መፍትሄ ለመስጠት አዲስና ዓለም አቀፋዊ የትብብር ሞዴል መገንባት እንደሚያስፈልግ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) ገለጹ።
የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ያዘጋጀው የ2025 ዳይመንድ ክለብ ሲምፖዚየም "አካታች ወደፊትን ለመፍጠር ዓለም አቀፍ የዲጂታል አመራር ማጠናከር" በሚል መሪ ሃሳብ ተካሄዷል።
በሲምፖዚየሙ መክፈቻ የኢኖቬሽን እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ ዲጂታል እድገት አበረታች መሆኑን ገልጸው፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች በዲጂታል መለያ ሥርዓቶች ውስጥ እየተካተቱ መሆኑን አስታውቀዋል።
የዲጂታል መሠረተ ልማቶች እየተስፋፉ እንዲሁም በኤሌክትሮኒክ የሚሰጡ የመንግስት አገልግሎቶች እያደጉ መምጣታቸውን በአብነት አንስተዋል።
በቅርቡ የፀደቀው የዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 ስትራቴጂ አካታች የኢኮኖሚ ዕድገትን ለማረጋገጥና የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማጎልበት ቁልፍ ሚና እንዳለው አጽንኦት ሰጥተዋል።
በዓለም ላይ ቴክኖሎጂን በአግባቡ አለመጠቀም አዲስ ፈተና የመፍጠር አቅም እንዳለው ጠቁመው፤ ይህን ፈተና ለመሻገር ሀገራት ትብብራቸውን ማጠናከር አለባቸው ብለዋል።
የመረጃ ግላዊነት፣ የሳይበር ደህንነት እና በሰው ሰራሽ አስተውሎት ላይ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች በአንድ ሀገር አቅም ሊፈቱ እንደማይችሉ አመላክተዋል።
በመሆኑም በዲጂታል ዘመን የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ለመከላከልና መፍትሄ ለመስጠት አዲስና ዓለም አቀፋዊ የትብብር ሞዴል መገንባት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል።
የአዲስ አበባ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ደረጄ እንግዳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ ዘመኑ ዲጂታል ቴክኖሎጂ ዓለምን ባልተጠበቀ ፍጥነት እየቀረጸ ያለበት ጊዜ መሆኑን ገልጸዋል።
ዩኒቨርሲቲው ባሉት የልህቀት ማዕከላት በመታገዝ በአህጉር ደረጃ ተጽዕኖ ፈጣሪ ለመሆን እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ተቋሙ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ላይ ያተኮረ ፈር ቀዳጅ ዩኒቨርሲቲ መሆኑን አስታውሰው፤ የአፍሪካን ቴክኖሎጂ የሚቀርጹ ተመራማሪዎች እና ዲጂታል መሪዎች ለማፍራት ቁርጠኛ መሆኑን ጠቁመዋል።
የዓለም አቀፉ የቴክኖሎጂ ፕሮፌሽናል ፕሮግራም ዳይሬክተር ፕሮፌሰር ጁንሴኦክ ሀዋንግ መድረኩን ላዘጋጁ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።
ከአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ጋር የተለያዩ ስራዎችን በጋራ እያከናወኑ መሆኑን ገልጸው፤ ትብብሩ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።
በቀጣይም ትልቁን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ዩኒቨርሲቲ ለመክፈት አመራሩ ቁርጠኛ መሆኑን አመላክተዋል።