ፖለቲካ - ኢዜአ አማርኛ
ፖለቲካ
በሞባይል ባንኪንግ ማጭበርበር ወንጀል የተሳተፉ ከ80 በላይ ዋነኛ ወንጀለኞች በሕግ ተጠያቂ ተደርገዋል
Jul 1, 2025 70
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 24/2017(ኢዜአ)፦ በሞባይል ባንኪንግ ማጭበርበር ወንጀል የተሳተፉ ከ80 በላይ ዋነኛ ወንጀለኞችን በሕግ ተጠያቂ ማድረጉን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ አስታወቀ። የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ ዘርፍ የ2017 በጀት ዓመት አፈጻጸም እና ቀጣይ አቅጣጫዎች ላይ ውይይት ተካሂዷል። የወንጀል ምርመራ የኦፕሬሽን ዋና መምሪያ ኃላፊና የወንጀል ምርመራ ቢሮ ኃላፊ ተወካይ አቶ ሙሊሳ አብዲሳ በበጀት ዓመቱ የተከናወኑ ተግባራትን በተመለከተ ማብራሪያ ሰጥተዋል። በሙስና፣ በህገ ወጥ የሰዎችና የጦር መሳሪያ ዝውውር፣ በኮንትሮባንድና አደንዛዥ ዕጽ ዝውውር የተጠረጠሩ ሰዎችን በቁጥጥር ስር በማዋል በህግ ተጠያቂ መደረጋቸውን አስታውቀዋል። ኮሚሽኑ ሕግን ለማስከበር በወሰደው እርምጃ 1 ሺህ ተጠርጣሪዎች ላይ የተለያየ መጠን ያለው የቅጣት ውሳኔ መተላለፉን አንስተዋል። በሞባይል ባንኪንግ ማጭበርበር የተሳተፉ ተጠርጣሪዎች ላይ ምርመራ በማድረግና የምርመራ መዝገብ በማጠናቀቅ ለጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ ቀርቦ ክስ እንዲመሰረትባቸው መደረጉን ተናግረዋል። እነዚህ ተጠርጣሪዎች ሀሰተኛ መታወቂያና በርካታ ሲም ካርዶችን በመጠቀም፣ ሆቴሎችና ማረፊያ ቤቶችን በመከራየት ዜጎችን በማጭበርበር ላይ ተሰማርተው የነበሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል። በዚህም በድርጊቱ ላይ የተሳተፉ ከ80 በላይ ዋነኛ ወንጀለኞች ላይ ምርመራ አድርጎ ክስ በመመስረት ወደ ማረሚያ ቤት እንዲወርዱ መደረጉንም አብራርተዋል። ከሀገር ውስጥና ከውጭ ኃይሎች ጋር በማበር በሽብር ወንጀል የተሳተፉ ተጠርጣሪዎችን ከብሄራዊ መረጃና ደህንነት እንዲሁም ከመከላከያ ሰራዊት ጋር በመሆን ለሕግ የማቅረብ ሥራ መከናወኑንም አስረድተዋል። በዚህም ከ450 በላይ ተጠርጣሪዎች በሰነድና በሰው ማስረጃ በማጣራት ክስ እንዲመሰረትባቸው የተደረገ ሲሆን በህግ ተጠያቂ መሆናቸውንም ገልጸዋል። በኮንትሮባንድና ሕገ ወጥ ጦር መሳሪያ ዝውውር ላይ የተሳተፉ 143 ተጠርጣሪዎች ለሕግ መቅረባቸውን ጠቁመው ካናቢስ፣ ኮኬይንን ጨምሮ የተለያየ መጠን ያላቸው አደንዛዥ ዕጾች ዝውውር ወንጀል የተሳተፉ ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር ውለው ተጠያቂ ተደርገዋል ብለዋል። እንደ ኃላፊው ገለጻ በበጀት ዓመቱ ከ6 ሺህ በላይ የምርመራ መዝገቦች ምርመራ ተጠናቆ ለፍትህ ሚኒስቴር የተላከ ሲሆን በዚህም በሀገርና በህዝብ ላይ ጉዳት በማድረስ የተጠረጠሩ ግለሰቦች ተጠያቂ እንዲሆኑ ማድረግ ተችሏል። አቶ ሙሊሳ አክለውም በዘረ መል/DNA/ ምርመራ ዘርፍም ከ300 በላይ የምርመራ ጉዳዮች መቅረባቸውን አስታውሰው ወቅቱንና ጥራቱን በጠበቀ መልኩ ምርመራ ተከናውኖ የተገኘው ውጤት ለሚመለከተው አካል ተደራሽ ተደርጓል ብለዋል። አጭበርባሪዎች ከባንክ የተደወለ በማስመሰል እያጭበረበሩ መሆኑን የገለጹት ሃለፊው ከባንክ ተደውሎ የሚሰጥ ምንም ዓይነት የባንክ አገልግሎት እንደሌለ ዜጎች ሊገነዘቡ እንደሚገባ አጽንኦት ሰጥተዋል። ዜጎች የሚስጥር ቁጥራቸውን ለሶስተኛ ወገን አሳልፈው መስጠት የለባቸውም ያሉት አቶ ሙሊሳ ህብረተሰቡ የአጭበርባሪዎች ሰለባ እንዳይሆን ሊጠነቀቅ እንደሚገባ አመልክተዋል።
ክልሉን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት የተገኙ ውጤቶችን ማስቀጠል ይገባል - አቶ አደም ፋራህ
Jul 1, 2025 89
ወላይታ ሶዶ ፤ሰኔ 24/2017 (ኢዜአ)፡-የደቡብ ኢትዮጵያ ክልልን የሰላም፣ የልማትና የመቻቻል ተምሳሌት ለማድረግ በተከናወኑ ተግባራት የተገኙ ውጤቶችን አጠናክሮ ማስቀጠል ይገባል ሲሉ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ማስተባበሪያ ማዕከል ሃላፊና የብልጽግና ፓርቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አደም ፋራህ ገለጹ። ''ጠንካራ ክልላዊ አንድነትና አብሮነት ለዘላቂ ሠላምና ብልጽግና" በሚል መሪ ሃሳብ ክልል አቀፍ የሠላም፣ የልማት እና የአንድነት ኮንፈረንስ በወላይታ ሶዶ ከተማ ተካሄዷል። በወቅቱም አቶ አደም ፋራህ እንዳሉት፤ በክልሉ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ዘርፎች እየተመዘገበ ያለውን ውጤት አጠናክሮ ለማስቀጠል ተደጋግፎ መስራት ይገባል። ኮንፈረንሱ በክልሉ ሰላም፣ ልማትና አንድነት ላይ አዎንታዊ ለውጥ በማምጣትና የህዝቡን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ የመልካም አስተዳደር ጉዳዮችን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማድረስ የሚያግዝ መሆኑንም ጠቁመዋል። በቀጣይ ጊዜያት ከፋፋይ ትርክቶችን በማስወገድ በመደመር ዕሳቤ ወንድማማችነት እና እህትማማችነትን አጠናክሮ በማስቀጠል የብልጽግና ጉዞን ማፋጠን ያስፈልጋል ብለዋል። የጋራ ማንነትን የሚያጎለብቱ ህብረ-ብሔራዊነትን ለማረጋገጥ ያለፈውን ቅሬታ በይቅርታ አልፎ ለወደፊት የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ መስራት እንደሚገባ ተናግረዋል። ጠንካራ ክልላዊ ተቋማትን ፈጥሮ በብቁ አመራር እንዲመሩ በማድረግ ብልሹ አሰራርን እና ሙስናን የሚጸየፍ ትውልድ መፍጠር እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል። የተለያዩ የልማት ኢኒሼቲቮችን ወደ ላቀ ደረጃ በማሸጋገር የክልሉን ብልጽግና ለማረጋገጥ መትጋት እንደሚገባም አስገንዝበዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ጥላሁን ከበደ በበኩላቸው ከክልሉ ምስረታ ማግስት ጀምሮ አብሮነትን የሚያጸኑ የጋራ ትርክቶችን ለማስረጽ የተሰራው ስራ ውጤት ማስመዝገቡን ተናግረዋል። ክልሉ ካለው የመልማት አቅም አንፃር ያልተሻገርናቸው በርካታ ነገሮች አሉ ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ በሁሉም መስክ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ መትጋት እንደሚገባ አሳስበዋል። ''ጠንካራ ክልላዊ አንድነትና አብሮነት ለዘላቂ ሠላምና ብልጽግና" በሚል መሪ ሃሳብ በወላይታ ሶዶ ከተማ ሲካሄድ የቆየው ክልል አቀፍ የሠላም፣ የልማት እና የአንድነት ኮንፈረንስ ዛሬ ተጠናቋል።
ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ የሥራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁ የሦስት አገራት አምባሳደሮችን አሰናበቱ
Jun 30, 2025 197
አዲስ አበባ፤ሰኔ 23/2017(ኢዜአ)፦የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀ ሥላሴ በኢትዮጵያ የሥራ ጊዜያቸውን ያጠናቀቁ የካናዳ፣የስዊዲንና የሳኡዲ አረቢያ አምባሳደሮችን አሰናበቱ። ፕሬዝዳንቱ ያሰናበቱት የካናዳ አምባሳደር ጆሽዋ ታባህ፣የስዊድን አምባሳደር ሃንስ ሄንሪክና የሳኢዲ አረቢያ አምባሳደር ፋሃድ አልሁማያዳኒ (ዶ/ር) ናቸው። ፕሬዝዳንት ታዬ ሦስቱም አምባሳደሮቹ በኢትዮጵያ ቆይታቸው ከአገራቱ ጋር በተለያዩ መስኮች የሁለትዮሽ ግንኙነትና ትብብር እንዲጠናከር ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋና አቅርበዋል። በተለይም የንግድና የኢንቨስትመንት ግንኙነት እንዲሳለጥ እንዲሁም በሌሎች የልማት የትብብር ዘርፎች ግንኙነቱ እንዲጠናከር ላደረጉት አስተዋጽዖም ምስጋናቸውን አቅርበዋል። አምባሳደሮቹ በሌሎች መስኮች ለአብነትም በመልሶ ማልማት ሥራዎች ጉልህ አስተዋጽኦ መደረጉን አንስተው፥ትብብሮች በቀጣይም ሊጠናከር እንደሚገባ ጠይቀዋል። በቀጣይ በተለይም ውጤታማ የንግድና ኢንቨስትመንት ግንኙነቶች ይበልጥ ሊጠናከሩ እንደሚገባ ጥሪ ማቅረባቸውን ውይይቱን የተከታተሉት የፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አምባሳደር ትዝታ ሙሉጌታ ለኢዜአ ገልጸዋል። አምባሳደሮቹ በበኩላቸው፥ በኢትዮጵያ ቆይታቸው አገራቸው ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን የሁለትዮሽ ግንኙነት ለማጠናከር በርካታ ሥራዎች መሥራታቸውንና በዚህም አመርቂ ውጤት መገኙቱን ጠቅሰዋል። የካናዳ አምባሳደር ጆሽዋ ታባህ በቆይታቸው የካናዳና ኢትዮጵያን የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ ለማስፋት የሚያስችሉ ውጤታማ ሥራዎች መከናወናቸውን ጠቅሰዋል። በተመሳሳይ የስዊድን አምባሳደር ሃንስ ሄንሪክ በቆይታቸው የኢትዮጵያ መንግሥት ቅድሚያ በሰጠባቸው መስኮች ትብብር በማድረግ አበረታች ሥራዎች ማከናወናቸውን አስረድተዋል። አምባሳደሮቹ በተለይም ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በኢትዮጵያ በተለያዩ ዘርፎች እየተዘመገቡ ያሉ ውጤቶች ተስፋ ሰጪ መሆናቸውንና መሰል ሥራዎችን ሊያጠናክር እንደሚገባ ተናግረዋል። በቀጣይም ግንኙነቱ ይበልጥ እንዲጠናከር የበኩላቸውን አስተዋጽዖ እንደሚያደርጉ አረጋግጠዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከዓለም አቀፍ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ(IAEA) ዋና ዳይሬክተር ጋር ተወያዩ
Jun 30, 2025 157
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 23/2017(ኢዜአ)፦ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከአለም አቀፍ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ(IAEA) ዋና ዳይሬክተር ማሪያኖ ግሮሲ ጋር ተወያይተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መልዕክት ዛሬ ጠዋት በሬይስ ኦፍ ሆፕ ጉባኤ ለመሳተፍ አዲስ አበባ ከመጡት የአለም አቀፍ የአቶሚክ ኃይል ኤጀንሲ(IAEA) ዋና ዳይሬክተር ማሪያኖ ግሮሲ ጋር ተገናኝተናል ብለዋል። የአለም አቀፉ አቶሚክ ኃይል በኢትዮጵያ የሚያደርገው ድጋፍ በካንሰር ሕክምና ክብካቤ፣ የእንስሳት ጤና፣ የፀፀ ፍላይ ዝንብ ማጥፊያ፣ በኒኩለር ኢንጂነሪንግ እና የቁጥጥር ማዕቀፎች ላይ ያተኮረ ነው ሲሉም ገልጸዋል። ውይይታችን በመካሄድ ላይ ባሉ ድጋፎች እና የወደፊት የትብብር እድሎች ላይ ያተኮረ ነበር ሲሉም አስታውቀዋል።
በቀበሌ ደረጃ መንግስታዊ አገልግሎት ተደራሽ መደረጉ ቀልጣፋ አገልግሎት ከማስገኘቱ ባለፈ የልማት ተሳታፊነታችንን እያሳደገ ነው -ነዋሪዎች
Jun 30, 2025 106
ጭሮ ፤ ሰኔ 23/2017(ኢዜአ)፦ በምዕራብ ሀረርጌ ዞን በቀበሌ ደረጃ መንግስታዊ አገልግሎት ተደራሽ በመደረጉ ለአስተዳደራዊ ጉዳዮቻቸው ፈጣን ምላሽ ከማስገኘቱ ባለፈ የልማት ተሳታፊነታቸው እያደገ መምጣቱን የዞኑ ዶባ ወረዳ ነዋሪዎች ገለጹ። በዞኑ በአዲስ መልክ ለተዘረጋው የቀበሌ አስተዳደር አገልግሎት መስጫ የሚውሉ ጽህፈት ቤቶች ግንባታ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት እየተደረጉ ነው። ነዋሪዎቹ በሰጡት አስተያየት ለህብረተሰቡ ቅርብ የሆኑ የቀበሌ መዋቅሮች ከዚህ ቀደም ትኩረት በማጣታቸው አገልግሎት ፍለጋ እስከ ወረዳ ማዕከላት ሲመላለሱ ቆይተዋል። በአሁኑ ወቅት የቀበሌ ፅህፈት ቤቶች በዘመናዊ መልኩ ተገንብተው ሙሉ አገልግሎት እያገኙ መሆኑን የተናገሩት በወረዳው የባቱ ቀበሌ ነዋሪ ኢብራሂም ሁሴን ናቸው። በጤና፣ በትምህርት፣ በግብርና እና መሰል ጉዳዮች አገልግሎት ፍለጋ እስከ ወረዳ ማዕከል ድረስ ሲመላለሱ እንደነበር ያነሱት አስተያየት ሰጪው አሁን ላይ እነዚህን አገልግሎቶች በአካባቢያቸው በሚገኝ ቀበሌ ጽህፈት ቤት በቅርበት አገልግሎት ማግኘት ጀምረዋል። ከዚህ ቀደም በወረዳ ደረጃ ብቻ የሚያገኙትን የመሬት ነክ እና ግብርና አገልግሎቶችን በቀበሌ ማግኘታቸው የልማት ተሳታፊነታቸውን እያሳደገ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ ሌላኛው አስተያየት ሰጪ አህመድ ኢብሮ ናቸው። ይህም የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮቻቸውን በማቃለል በአካባቢያቸው በሚከናወኑ የልማት ስራዎች ውስጥ ተሳትፏቸው እንዲጨምር ማድረጉንም ተናግረዋል። በብልጽግና ፓርቲ የዶባ ወረዳ ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ሙዘይን ከማል እንዳሉት በወረዳው የመልካም አስተዳደር ችግሮችን ለመቅረፍ በተጀመረው የቀበሌ አገልግሎት ማጠናከር ስራ ህብረተሰቡ በቅርበት አገልግሎት እንዲያገኝ ማድረግ ተችሏል። ሙሉ አገልግሎቶች ለህብረተሰቡ በቅርበት እንዲሰጡ በመደረጉም አርሶ አደሩ ከግብርና ስራው እንዳይስተጓጎል ሁሉንም መንግስታዊ አገልግሎት በቅርበት እንዲያገኝ ማድረጉን ተናግረዋል። በምዕራብ ሐረርጌ ዞን በሚገኙ 15 ወረዳዎችና አምስት ከተሞች የቀበሌ አደረጃጀቶችን በማጠናከር 3 ሺህ 522 ባለሙያዎች ተመድበው አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ ወይዘሮ ኢክራም ጠሀ ናቸው። በዚህም 512 የቀበሌ ፅህፈት ቤቶች በዘመናዊ መልኩ እንዲገነቡ መደረጉን አመልክተዋል።
መንግሥት የሕዝቡን ጥያቄ ለመመለስ ዛሬም እንደ ትናንቱ በትጋት ይሠራል - የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
Jun 29, 2025 220
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 22/2017(ኢዜአ)፦መንግሥት የሕዝቡን ጥያቄ ለመመለስ ዛሬም እንደ ትናንቱ በትጋት እንደሚሰራ የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አስታወቀ። አገልግሎቱ ዛሬ ባወጣው መግለጫ የአማራ ክልል ሕዝብ ባለፉት ጥቂት ዓመታት መክፈል የማይገባውን ውድ ዋጋ በጥቂት ጥቅመኞች ምክንያት እየከፈለ መሆኑን ገልጿል። የፋኖን ታሪካዊ አነሣሥና ዓላማ ባልተከተለ አግባብ ራሳቸውን በፋኖ ስም የሚጠሩ ፅንፈኛ ኃይሎች በቀሰቀሱት ግጭትም የአማራ ክልል ሰላም እና ልማት ክፉኛ መጎዳቱን ጠቁሟል። መንግሥት ባለፉት ዓመታት ግጭቶችን ለማስወገድ በርካታ አማራጮችን ሲከተል መቆየቱ የሚታወስ ነው ያለው አገልግሎቱ ጥያቄ ያላቸዉ አካላትን በማቅረብ ለማነጋገር እና ለመደራደር በርካታ ጥረቶችን ማድረጉን ገልጿል ። የመንግስት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው ቀርቧል፡- የአማራ ክልል ሕዝብ ባለፉት ጥቂት ዓመታት መክፈል የማይገባዉን ውድ ዋጋ በጥቂት ጥቅመኞች ምክንያት እየከፈለ ይገኛል፡፡ የፋኖን ታሪካዊ አነሣሥ እና ዓላማ ባልተከተለ አግባብ ራሳቸዉን በፋኖ ስም የሚጠሩ ፅንፈኛ ኃይሎች በቀሰቀሱት ግጭት የአማራ ክልል ሰላም እና ልማት ክፉኛ ተጎድቷል፡፡ ፋኖ ሀገር በባዕድ ወራሪ እጅ በወደቀችበት እና ማእከላዊ መንግሥት በግዞት በቆየበት ወቅት ሀገርን ለማዳን የተደረገ ተጋድሎ የተመራበት ድንቅ ስያሜ ነው፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ግን የሀገሩን እና የክልሉን መንግሥት ለማፍረስ እና የባዕዳንን ተልእኮ ለማሳካት የተደራጁ ቡድኖች መጠሪያ ተደርጎ ሀገርን እና ሕዝብን ውድ ዋጋ አስከፍሏል፡፡ በሚሊዮኖች የሚቈጠሩ ታዳጊዎችን ከትምህርት ገበታ ነጥሏል፡፡ ሕዝብን ከልማት እንቅስቃሴዎች አሰናክሏል። የአማራ ክልል ሕዝብም የግጭት ጠማቂዎቹን እና የተላላኪዎቹን አጀንዳ በሚገባ ተገንዝቦ መንግሥት ሰላም እንዲያሰፍን በተደጋጋሚ ጥያቄዎችን በተለያዩ አግባቦች ሲያቀርብ መቆየቱ የሚታወስ ነው፡፡ የአማራ ክልል ሕዝብ ክልሉን ከግጭት እና ሥርዐት አልበኝነት ለማውጣት በየአካባቢዉ ተሰባስቦ ምክክር እና ውይይት አካሂዷል። የክልሉ ሕዝብ ጥያቄዎች በብሔራዊ ምክክር ኮሚሽን በአጀንዳነት እንዲያዙ አድርጓል፤ ራሱን ፋኖ ብሎ የሚጠራዉ ቡድን ትክክለኛ የነፃነት ታጋይ መስሎት የተቀላቀለ ወጣት ወደ ሰላማዊ ሕይወቱ እንዲመለስ በሀገር ሽማግሌዎች እና የሃይማኖት አባቶች ለምኗል፡፡ ከዚህም መሳ ለመሳ የፌደራል የፀጥታ ተቋማት እና የክልሉ የፀጥታ መዋቅር የክልሉን ሰላም ለማረጋጥ ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፤ መሥዋዕትነትም ከፍለዋል፤ እየከፈሉም ነው፡፡ በዚህም በክልሉ አብዛኞቹ አካባቢዎች ሰላም ማስፈን ተችሏል፡፡ በተፈጠረው አስቻይ ሁኔታም የክልሉ ሕዝብ ከልማት ጥረቶች ወደ ኋላ እንዳይቀር በርካታ የልማት ሥራዎች ተከናውነዋል። ይሁን እንጅ በፀጥታ ኃይላችን ጥረት እና በሀገር ሽማግሌዎች ተማፅኖ አንጻራዊ ሰላም ቢሰፍንም ሕዝቡ በሚሻዉ ልክ የክልሉ ሰላም ሙሉ ለሙሉ አልተረጋገጠም፤ የዜጎች እንቅስቃሴ ከእገታና ዘረፋ ስጋት በምልዓት አልተላቀቀም፡፡ የነገ ሀገር ተረካቢዎች በተሟላ መልኩ ወደ ትምህርት ገበታ አልተመለሱም፡፡ የልማት እንቅስቀሴዎች ሕዝብ እና መንግሥት በሚሹት ልክ እንዲፋጠኑ ምቹ ድባብ አልሰፈነም፡፡ በዚህ ምክንያት ሕዝቡ ብሶቱን ለመንግሥት ጎላ አድርጎ ለማሰማት በተለያዩ ከተሞች ሰላማዊ ሰልፎችን አካሂዷል፡፡ በሰላማዊ ሰልፎቹ መንግሥት የክልሉን ሰላም በማረጋገጥ ልማትን እንዲያጠናክር ሕዝቡ ጠይቋል፡፡ መንግሥት የውስጥ ባንዳዎችን እና የውጭ ኃይሎችን አደብ እንዲያስገዛለት፣ ልጆቹ ወደ ትምህርት ገበታ እንዲመለሱለት፣ ማሳውን ወደ መጎልጎልና ማረስ እንዲሰማራ፣ በኑሮው በሰላም ወጥቶ መግባት እንዲችል ምቹ ድባብ እንዲፈጠርለት፣ ሰላሙን በጋራ ለመጠበቅ እንደተዘጋጀ እና መንግሥት ሕግ ለማስከበር የጀመረዉን ጥረት በፅናት እንደሚደግፍ በሰላማዊ ሰልፎቹ ገልጿል፡፡ መንግሥት ባለፉት ዓመታት ግጭቶችን ለማስወገድ በርካታ አማራጮችን ሲከተል መቆየቱ የሚታወስ ነው፡፡ ጥያቄ ያላቸዉ አካላትን በማቅረብ ለማነጋገር እና ለመደራደር በርካታ ጥረቶችን አድርጓል፡፡ በተደጋጋሚ የይቅርታ እና ምሕረት ጥሪዎችን አቅርቧል፡፡ በዚህም በርካታ በስሕተት የጥፋት ኃይሎችን ተቀላቅለዉ የነበሩ አካላት እጃቸዉን በመስጠት ሕይወታቸዉን አትርፈዋል፤ ሕዝቡን ለመካስ የሚያስችል የተሐድሶ ሥልጠናም አግኝተዋል፡፡ ነገር ግን አሁንም ጥቂት ጥቅመኞች የሕዝቡን ሰላም እያወኩ የባዕዳንን ተልእኮ ለማሳካት እየተወራጩ ይገኛሉ፡፡ መንግሥት የሕዝቡን የሰላም፣ የልማት እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ለመመለስ ዛሬም እንደትናንቱ ዝግጁ ነው፤ መንግሥታዊ ኃላፊነቱም ነው፡፡ የአማራ ክልል ሕዝብን ጥያቄዎች ለመመለስ ከክልሉ ሕዝብ፣ ከክልሉ አስተዳደር እና የፀጥታ ኃይል ጋር በመቀናጀት መንግሥት የላቀ ጥረት ያደርጋል፡፡ ሕዝቡ ከመንግሥት ጋር በመቀናጀት ሰላሙን ለመጠበቅ ያሳየዉን ቁርጠኝነትም ያደንቃል፡፡ የሰላም በሮችን ዛሬም ክፍት አድርጎ እየጠበቀ የሕዝቡን የሰላም እና የልማት ጥያቄ ለመመለስ ከመቼዉም ጊዜ በላቀ ደረጃ ዝግጁ መኾኑንም መንግሥት ያረጋግጣል፡፡ የሰላም አማራጮችን የማይቀበሉ አካላትን በክልሉ የፀጥታ መዋቅር እና በፌደራል መዋቅር አማካኝነት አደብ በማስገዛት የሕዝቡን ሰላም ለማረጋገጥ ይሠራል፡፡ ሕዝቡ በአደባባይ ያቀረባቸዉን ጥያቄዎች ከሕዝብ ጋር ለመመለስ ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋል፡፡ ሕዝቡ በሠለጠነ አግባብ ሐሳቡን በመግለጹም መንግሥት ምስጋና ያቀርባል፡፡ ሰኔ 22 ቀን 2017 ዓ/ም የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
መንግስት ህግ በማስከበር ሰላምና ልማትን ለማጽናት እያደረገ ላለው ጥረት ተሳትፏችንን እናጠናክራለን
Jun 29, 2025 153
ደብረ ብርሃን፣ደብረ ማርቆስ፣ገንዳ ውሃና ወልዲያ፤ሰኔ 22/2017(ኢዜአ)፦መንግስት ህግ በማስከበር ሰላምና ልማትን ለማጽናት እያደረገ ላለው ጥረት ተሳትፏቸውን እንደሚያጠናክሩ በአማራ ክልል የተለያዩ ከተሞች ነዋሪዎች ገለጹ። በክልሉ ደብረ ብርሃን፣ደብረ ማርቆስ፣ መተማ ዮሐንስ እና ወልዲያ ከተሞች ሰላምን የሚደግፉና ጽንፈኝነትን የሚያወግዙ ህዝባዊ ሰልፎች ዛሬ ተካሂደዋል። በደብረ ብርሃን ከተማ በተካሄደ ህዝባዊ ሰልፍ የተሳተፉት አቶ ከፍያለው ግርማ በሰጡት አስተያየት የሰላም እጦት ችግር በውይይትና በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ የበኩላቸውን ለመወጣት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ታጥቀው በጫካ ያሉ ሀይሎች የመንግስትን የሰላም አማራጭ ተቀብለው ወደሰላም እንዲመጡና የሰላም ፍላጎታቸውን ለማሰማት በሰልፉ መታደማቸውን ተናግረዋል። ኑሮውን ሎተሪ አዙሮ በመሸጥ የሚመራው ሌላው የሰልፉ ተሳታፊ በፍቃዱ በለጠ በበኩሉ፥ሰርቶ ለማደግና ለመለወጥ ሰላም ወሳኝ መሆኑን ገልጾ፣ ሰላም እንደሚፈልግ በጋራ ድምጹን ለማሰማት በሰልፉ መሳተፉን ገልጿል። የደብረብርሃን ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ በድሉ ውብሸት በሰልፉ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፥ የሰላም እጦት ችግሩን ለመፍታት መንግስት ህግ ከማስከበር ጎን ለጎን ለታጠቁ አካላት በተደጋጋሚ የሰላም ጥሪ ማቅረቡን አስታውሰዋል። የጥፋት ሀይሎች በህዝብና በሀገር ላይ እየፈጸሙት ያለውን የጥፋት ተግባር በማቆም የህዝብን ጽኑ የሰላም ፍላጎት በማክበር የመንግስትን የሰላም አማራጭ ሊቀበሉ ይገባል ብለዋል። በተያያዘ ዜና በደብረ ማረቆስ ከተማ በተካሄደ ህዝባዊ ሰልፍ ላይ የተሳተፉት ወይዘሮ እታገኝ አዳነ፥ ባለፉት ሁለት ዓመታት ያሳለፍነው ችግር እንዲያበቃ እንፈልጋለን፤ የእኛ ፍላጎት ዘላቂ ሰላምና ልማት ነው ብለዋል። ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ አካላት የመንግስትን የሰላም ጥሪ በመቀበል ወደ ሰላም እንዲመጡ እንፈልጋለን ያሉት ወይዘሮ እታገኝ፣ ለአካባቢው ሰላም መንግስት ከሚያደርገው ጥረት በተጨማሪ የበኩላቸውን ሚና ለመወጣት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል። ሌላዋ ተሳታፊ ወይዘሮ አንለይ ተረፈ በበኩላቸው፥ ሰው በሰላም ወጥቶ መግባትና ሰርቶ መብላት የሚችለው ሰላም ሲኖር ነው ብለዋል። ሌላው የሰልፉ ተሳታፊ አቶ በላይ እንየው በበኩላቸው፥ በግጭት ሰቆቃ፣ መከራና ስቃይ እንጂ የሚመጣ ለውጥ የለም ፤ ሰላምን እንደምንፈልግ በይፋ ለመግለጽ ዛሬ በሰልፉ ላይ ተገኝተናል ብሏል። አንድነታችንን በማጠናከር ሰላምና ልማትን ማጽናት የትኩረት አቅጣጫችን ነው ያሉት ደግሞ የደብረ ማርቆስ ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ተሾመ ዋለ ናቸው። "ህዝቡ ለሰላሙ ያሳየውን ቁርጠኝነት በማስቀጠል በከተማው የተጀመረው የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ፣የኮሪደር ልማትና ሌሎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎችን በፍጥነት በማጠናቀቅ ለአገልግሎት እናበቃለን ብለዋል። የምስራቅ ጎጃም ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ኑርልኝ ብርሃኑ በበኩላቸው፥ ህብረተሰቡ በተባበረ ድምጽ ጽንፈኞች ከጥፋት ተግባራቸው እንዲታቀቡ ያሳየው ቁርጠኝነት ትልቅ አቅም ነው ብለዋል። በሌላ በኩል በመተማ ዮሐንስ ከተማ በተካሄደ ሰልፍ የተሳተፉት አቶ ጥላሁን ንጉሴ በበኩላቸው፥በአካባቢው ጸጥታ ችግር ምክንያት ህዝቡ በሰላም ወጥቶ መግባት ቀርቶ የተሻለ ህክምና እንኳ ለማግኘት ተቸግሮ እንደነበር አስታውሰዋል። መንግስት የጀመረውን የህግ የማስከበር ሥራ እንደሚደግፉ ገልጸው፣ በጫካ ያለው ሃይል የመንግስትን የሰላም ጥሪ እንዲቀበልና ሰላምን እንደምንፈልግ መልዕክት ለማስተላለፋ ሰልፍ መውጣታቸውን ተናግረዋል። ሌላኛዋ የሰልፉ ተሳታፊ ወይዘሮ ሲሳይነሽ ይርጋ በበኩላቸው፥ ፅንፈኝነት የነገ ሀገር ተረካቢ ህፃናትን ጭምር ሰለባ እያደረገ በመሆኑ ከመንግስት ጎን ሆነው ለመታገል ቁርጠኛ መሆናቸውን ነው የገለጹት። ጽንፈኝነትን ማውገዝ ብቻ ሳይሆን መታገልም ያስፈልጋል ያሉት ደግሞ የመተማ ዮሐንስ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ሀብቴ አዲሱ ናቸው። መንግስት ዘላቂ ሰላምን በማስፈን ልማትን ለማረጋገጥ የጀመረው ሥራ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ህዝቡ ከመንግስት ጎን ሆኖ የሚያደርገውን አስተዋጾ እንዲያጠናክርም አስገንዝበዋል። በተመሳሳይ በወልዲያ ከተማ በተካሄደ ሰልፍ ላይ የተገኙ ተሳታፊዎች ባለፉት ሁለት ዓመታት ከሰላም እጦት ያተረፉት የሰዎች ሞት፣ እገታ፣ ዝርፊያና ስደትን ብቻ መሆኑን ተናግረዋል። መንግስት ሰላም እንዲጠናከር ታጥቀው የሚንቀሳቀሱ ሀይሎች ወደሰላም እንዲመጡ ያቀረበውን ጥሪ እንደሚደግፉ ገልጸው፣ የጥፋት ሀይሎች ጥሪውን በመቀበል ወደሰላም እንዲመጡ ጠይቀዋል። የወልድያ ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ዱባለ አብራሬ በበኩላቸው፥የጽንፈኞች እኩይ ሴራ የልማት ሥራን እንዳያደናቅፍ ጠንክሮ መታገል ይገባል ብለዋል። የታጠቁ ሃይሎችም የህዝብን ድምጽ በመስማትና በማክበር መንግስት በተደጋጋሚ ያቀረበውን የሰላም አማረጭ ተቀብለው ህዝባቸውን እንዲክሱም ከንቲባው አስገንዝበዋል። በተለያዩ ከተሞች በተካሄዱ ህዝባዊ ሰልፎች ላይ የተሳተፉ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ለሰላም ጽኑ ፍላጎት እንዳላቸውና ጽንፈኝነት ሀገርና ህዝብን ስለሚጎዳ ለሰላማቸው ከመንግስት ጎን እንደሚቆሙ ገልጸዋል።
ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ እና ልማት እንዲፋጠን ድጋፋችንን እናጠናክራለን
Jun 29, 2025 167
ባህርዳር፤ ሰኔ 22/2017 (ኢዜአ) በአማራ ክልል ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ እና የልማት ስራ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ድጋፋቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ በባህርዳር ከተማ የህዝባዊ ሰልፍ ተሳታፊዎች ገለጹ። በባህርዳር ከተማ ‘‘ሀገርን ለማፅናት እና ለማበልፀግ ከመንግስት ጎን እንሰለፋለን’’ በሚል መሪ ሀሳብ ሰላምን የሚደግፍ ህዝባዊ ሰልፍ ዛሬ ተካሂዷል። ከሰልፉ ተሳታፊዎች መካከል ወጣት ትዕዛዙ ገብረኢየሱስ ለኢዜአ እንደገለጸው በክልሉ ዘላቂ ሰላምና ልማትን ማረጋገጥ ለህዝቡ ያለው ፋይዳ ከፍተኛ ነው። በክልሉ አሁን ላይ ባለው ሰላም በከተማው ልማት እንዲፋጠንና የወጣቶች ተጠቃሚነት እያደገ እንዲመጣ ማስቻሉን ገልጿል። የተገኘው ሰላም ዘላቂ እንዲሆንና የልማት ስራዎች እንዲጠናከሩ ተሳትፏችንን እናጠናክራለን " ያለው ወጣት ትዕዛዙ የታጠቁ ሀይሎች የመንግስትን የሰላም ጥሪ በመቀበል ወደ ሰላም እንዲመጡ ጠይቋል ። "የሰላም እጦት የሚያስከትለው ጥፋት በመሆኑ ለሰላም ዘብ ለመቆም ቆርጠን ተነስተናል" ያሉት ደግሞ የሰልፉ ታዳሚ ወይዘሮ አስረሱ ጌትነት ናቸው። በከተማው አሁን ላይ ባለው ሰላም ተስፋ ሰጭ የልማት ስራዎች እየተፋጠኑ መሆኑን ተናግረዋል። "በጫካ ላሉ የታጠቁ ሀይሎች የመንግስትን የሰላም ጥሪ ተቀብለው ወደ ሰላም ሊመጡ ይገባል" ሲሉ መልእክት አስተላልፈዋል። ‘‘በክልላችን ዘላቂ ሰላምና ልማት እንዲረጋገጥ ድምፃችንን ለማሰማት በሰልፉ ተሳትፈናል ’’ ያለው ደግሞ ወጣት ሳለአምላክ አድማሱ ነው። ሰላም ለአንድ ወገን የሚተው አለመሆኑን ጠቁሞ "ሁላችንም ከመንግስት ጎን በመሰለፍ ዘላቂ ሰላምን በማስፈን ልማት እንዲረጋገጥ በቁርጠኝነት ልንሰራ ይገባል" ብሏል። የባህርዳር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጎሹ እንዳላማው የከተማው አስተዳደር ሰላምን በማጽናት ልማትን ለማረጋገጥ በልዩ ትኩረት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል። "ፅንፈኛው ኃይል በክልሉና በከተማችን ሰብአዊና ቁሳዊ ጉዳት አድርሷል" ያሉት አቶ ጎሹ ህፃናት ከትምህርት ገበታ እንዲርቁ ማድረጉን ጠቅሰዋል። የፅንፈኛው ሀይል የክልሉን ልማትና ዕድገት ወደ ኋላ የሚጎትት በመሆኑ ህብረተሰቡ በዛሬው ሰልፍ ጽንፈኝነትን በማውገዝ የመንግስትን የሰላም ጥሪ የደገፈበት መሆኑን ተናግረዋል ። ጫካ የሚገኙ ኃይሎች የሰላም ጥሪን ተቀብለው ህዝባቸውን እንዲክሱም አሳስበዋል። በከተማው ሰላምን ዘላቂ ለማድረግና ልማትን ለማፋጠን እየተደረገ ባለው ጥረት የህብረተሰቡ ድጋፍ ከፍተኛ መሆኑን ጠቁመው ይኽው የህዝቡ ተሳትፎ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል ። በሰልፉ ላይ የሃይማኖት አባቶች፣ የሃገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶች፣ ሴቶችና ሌሎች የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
የመንግስትን የልማት እቅዶች በመደገፍ እና የሰላም ጥረቶች በማገዝ የድርሻችንን እንወጣለን
Jun 29, 2025 129
ደሴ፤ሰኔ 22/2017(ኢዜአ)፦ የመንግስትን የልማት እቅዶች በመደገፍና የሰላም ጥረቶች በማገዝ የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ በደሴ ከተማ በተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የተሳተፉ ነዋሪዎች ተናገሩ። በደሴ ከተማና አካባቢው ሰላምና ልማትን የሚደግፍና ፅንፈኝነትን የሚያወግዝ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሃዷል። ከሰላማዊ ሰልፉ ተሳታፊዎች መካከል አቶ ዘሪሁን ማንደፍሮ፣ ወይዘሮ መብራት ፈለቀ እና አቶ ሰለሞን አሰፋ፤ ከምንም በላይ ሰላምና ልማታችንን አጥብቀን እንሻለን ጸረ ሰላም ቡድኖችን ደግሞ እናወግዛለን ብለዋል። የደሴና አካባቢው ሰላም አስተማማኝ የሆነው በህዝቡ ትብብርና ጥረት፣ በፀጥታ አካላት ትጋት መሆኑን አንስተው ይህንኑ አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉም ተናግረዋል። በመሆኑም የመንግስትን የልማት እቅዶችን በመደገፍና የሰላም ጥረቶችን በማገዝ የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ አረጋግጠዋል። የመንግስት የሰላምና የልማት ጥረት የሚደገፍ በመሆኑ ለሰላማዊ ሰልፍ መውጣታቸውን ተናግረው ለእኩይ ዓላማ የሚንቀሳቀሱ አካላት ከድርጊታቸው ሊታቀቡ እንደሚገባም አንስተዋል። በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በህዝብ ስም እየማሉ ግድያ፣ ዘረፋ፣ እገታና ውንብድና የሚፈጽሙ ጽንፈኞችን በፅኑ እናወግዛለን፤ ለሰላማችንም ዘብ እንቆማለን ሲሉ ተናግረዋል። የደሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ሳሙኤል ሞላልኝ፤ በሁሉም አካባቢዎች ህብረተሰቡ አንድነቱን በማጠናከር እያሳየ ያለውን ሁለንተናዊ ድጋፍና ተሳትፎ አድንቀዋል። ከውጭ ታሪካዊ ጠላቶች ጋር በማበር ሀገርን ለማፍረስ የሚሰሩ ቡድኖች ከክህደት እና ሸፍጥ በመውጣት ለሀገር ልማትና እድገት በጋራ እንዲቆሙም ጠይቀዋል። የተጀመሩ ሀገራዊ የልማት እቅዶችን ከዳር በማድረስ ሀገራዊ ህብረ ብሄራዊ አንድነትና ሰላምን በማፅናት ሀገር መገንባት ይጠበቅብናል ብለዋል። በዛሬው እለት ከደሴ ከተማ በተጨማሪ በኮምቦልቻ፣ ሐይቅ እና ሌሎችም ከተሞች ተመሳሳይ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፎች ተካሂደዋል።
ሰላማችንን በማጽናት በከተማችን የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት እንዲበቁ የድርሻችንን ለማበርከት ዝግጁ ነን
Jun 29, 2025 128
ጎንደር ፤ሰኔ 22/2017 (ኢዜአ) ሰላማችንን በማጽናት በከተማችን የተጀመሩ የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ የድርሻችንን ለማበርከት ዝግጁ ነን ሲሉ የጎንደር ከተማ ነዋሪዎች ተናገሩ፡፡ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተሳተፉበት ሰላምን የሚደግፍና ጽንፈኝነትን የሚያወግዝ ህዝባዊ ሰልፍ ዛሬ በጎንደር ከተማ ተካሂዷል፡፡ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ ነዋሪዎች እንደተናገሩት ጎንደር በከፍተኛ የልማት ሥራ ላይ ትገኛለች፤ ሰላሙንና ልማቱን ለማስቀጠል ደግሞ እኛ ነዋሪዎች ከመቼውም ጊዜ በላይ ቁርጠኞች ነን ሲሉ ተናግረዋል "ጎንደር የቀደመ ገናና ስሟንና ታሪኳን የሚመጥን የመልማት እድል ያገኘችው አሁን ነው" ያሉት በህዝባዊ ሰልፉ ላይ የተሳተፉት አቶ ጌትነት መንግስቱ ናቸው፡፡ ከተማዋ ያገኘችው ዘርፈ ብዙ የልማት እድሎች ለህዝቡ የዘመናት የልማት ጥያቄ መሰረታዊ ምላሽ የሚሰጡ በመሆናቸው ለሰላም ዘብ በመቆም ልማቱን ለማስቀጠል የድርሻቸውን ለማበርከት መዘጋጀታቸውን ተናግረዋል፡፡ ሌላዋ የሰልፉ ተሳታፊ ወይዘሮ አለምነሽ ብርሃኑ በበኩላቸው በከተማው እየተካሄዱ የሚገኙ የኮሪደር ልማትና የአጼ ፋሲል አብያተ መንግስት እድሳትና ጥገና ሥራዎች ታሪካችንን ያደሱ አኩሪ የልማት ተግባራት ናቸው ብለዋል፡፡ "ጎንደር በአሁኑ ወቅት ያገኘችው የልማት ዕድል በምንም መንገድ ወደኋላ ሊመለስና ሊቀለበስ የማይችል ነው" ያሉት ወይዘሮ አለምነሽ ለልማትና ለሰላም ጸር የሆነውን ጽንፈኝነት ለመታገል ቁርጠኛ መሆናቸውን ገልጸዋል። በፌደራልና በክልሉ መንግስት ድጋፍ በከተማችን እየተካሄዱ ያሉ የልማት ፕሮጀክቶች በርካታ ወጣቶችን የሥራ እድል ተጠቃሚ ለማድረግ አስችሏል ያለው ደግሞ ወጣት መሃመድ አብዲ ነው፡፡ በለውጥና በአዲስ የእድገት ጎዳና ላይ የምትገኘው ሀገራችን ወጣቶች በሃገራቸው ብሩህ ተስፋ እንዲሰንቁና ለልማትና ሰላም ማስፈን እንዲተጉ መነሳሳት ፈጥሯል ብሏል። የጎንደር ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ቻላቸው ዳኘው በሰልፉ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት በጎንደር ከተማ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶች መጀመራቸውን አስታውሰዋል። የከተማው ህዝብ ከዳር አስከ ዳር በመነሳት የልማት ሥራዎችን በገንዘብ፣ በጉልበቱና በእውቀቱ እየደገፈ መሆኑን የጠቆሙት ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው፣ "ጎንደር ለሰላም ዋጋ የምትሰጥ ከተማ ነች" ብለዋል፡፡ ለከተማዋ እድገት አስተዋጽኦ ላደረጉ የፌደራልና የክልሉ አመራሮች እንዲሁም በሀገር ውስጥና በውጭ ላሉ ወገኖችም ምስጋና አቅርበዋል። በህዝባዊ ሰልፉ ላይ የመንግስት ሠራተኞች፣ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶችን ጨምሮ የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፈዋል።
የታጠቁ ቡድኖች የህዝብን የሰላም ፍላጎት እንዲያከብሩ እና የመንግስትን የሰላም ጥሪ እንዲቀበሉ ተጠየቀ
Jun 29, 2025 123
ሰቆጣ ፤ ሰኔ 22/2017(ኢዜአ)፦ የታጠቁ ቡድኖች የህዝብን የሰላም ፍላጎት እንዲያከብሩ እና የመንግስትን የሰላም ጥሪ እንዲቀበሉ የሰቆጣ ከተማ ነዋሪዎች በሰላማዊ ሰልፍ ጠየቁ። በዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር የተለያዩ ከተሞች ሰላምን የሚደግፍና ጽንፈኝነትን የሚያወግዝ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ ተካሂዷል። በሰቆጣ ከተማ በተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የተገኙት ቄስ መኳንቱ ወርቁ እና አቶ አወል መሃመድ፤ የሰላምን መንገድ በመግፋት በግጭትና ጦርነት የሚንቀሳቀሱ ቡድኖች ህዝቡን ብዙ ዋጋ እያስከፈሉትና ችግር ላይ እየጣሉት መሆኑን አንስተዋል። ከምንም በላይ በሰላም ወጥተን መግባት፣ ሰርተን መኖርና ልጆቻችንን ማስተማር እንሻለን ያሉት ሰልፈኞቹ የጦርነት ቅስቀሳ የሚያደርግን አካል በፅኑ እንቃወማለን ብለዋል። የሰላም ጉዳይ የሁላችንም የጋራ አጀንዳ በመሆኑ ሰላምን በማፅናት ግጭትና ጦርነትን በመጥላት ወደ አደባባይ ወጥተናል ሲሉም ተናግረዋል። በመሆኑም የታጠቁ ቡድኖች የህዝብን የሰላም ፍላጎት እንዲያከብሩና የመንግስትን የሰላም ጥሪ እንዲቀበሉ ሰልፈኞቹ ጠይቀዋል። በዚሁ መርሃ ግብር ላይ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የዋግ ኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር ተቀዳሚ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሃይሉ ግርማይ፤ የመንግስት ፍላጎትና ተደጋጋሚ ጥረት ሰላም መሆኑን በማንሳት ለዚህም ተደጋጋሚ ጥሪ መቅረቡን አስታውሰዋል። በመሆኑም የህዝቡ ጥያቄ ሰላም በመሆኑ ይህንኑ በማክበር የታጠቁ ቡድኖች ሳይውሉ ሳያድሩ እድሉን እንዲጠቀሙበት ጠይቀዋል። ከዚህ ባለፈ መንግስት ሰላም የማስከበር ሃላፊነት ያለበት መሆኑን አንስተው በተጠናከረና በተቀናጀ መልኩ የሚሰራ መሆኑን አረጋግጠዋል። የሰቆጣ ከተማ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ጌትነት እሸቱ በበኩላቸው በአሁኑ ወቅት በከተማው ያለው አስተማማኝ ሰላም የህዝቡ የረዥም ጊዜ ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ አስችሏል ብለዋል። በመሆኑም ታጥቀው ጫካ የገቡ ቡድኖች የህዝቡን እና የመንግስትን የሰላም ጥሪ በመቀበል ከጥፋት ወደ ልማት እንዲመለሱ ጠይቀዋል።
በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ብሔራዊ ጥቅምን በማስጠበቅ እያደረጉ ያለውን አስተዋጽኦ ማጠናከር ይገባቸዋል
Jun 29, 2025 94
አዲስ አበባ ፤ ሰኔ 22/2017(ኢዜአ)፦ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የሀገራቸውን ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅ እና በልማት እያደረጉ ያለውን አስተዋጽኦ የበለጠ እንዲያጠናክሩ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዲማ ኖጎ (ዶ/ር) ጥሪ አቀረቡ። የኢትዮጵያ ዳያስፖራ አገልግሎት ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ እና ከውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ ሃላፊዎች የዳያስፖራውን ተሳትፎ በሚያጠናክሩ ጉዳዮች ላይ ምክክር አካሂዷል። የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢው ዲማ ኖጎ (ዶ/ር) ዳያስፖራው የሀገሩን ብሔራዊ ጥቅም በማስከበርና በልማት በመሳተፍ ሚናው የጎላ እንደሆነ አንስተዋል። በተለያየ ዓለም የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ብሔራዊ ጥቅምን በሚያስከብሩ ጉዳዮች ላይ በመሳተፍ ለሀገራቸው በተለያየ ዘርፍ የሚያደርጉትን አስተዋፅኦ እንዲያጠናክሩ ጠይቀዋል። ዳያስፖራው በሪሚታንስ፣ ኢንቨስትመንትና በበጎ አድራጎት እያደረገ ያለውን አስተዋጽኦ የበለጠ ለማሳደግ በሚወጡ ህጎች የዳያስፖራውን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ትኩረት እንዲሰጡ ይደረጋል ብለዋል። የዳያስፖራ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አምባሳደር ፍጹም አረጋ እንደተናገሩት በተለያየ የዓለም ክፍል የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለሀገራቸው የሚያበረክቱት አስተዋጽኦ እየጨመረ ነው። በኢንቨስትመንት፣ በሪሚታንስ፣ በበጎ አድራጎት፣ በልማት ስራዎች ላይ የሃሳብና የገንዘብ ተሳትፎ በማድረግ፣ በቱሪዝምና ሌሎች ዘርፎች ተሳትፏቸው እየጨመረ መምጣቱን ነው ያስረዱት። በሀገር የኢኮኖሚ እድገት ላይ ያላቸውን ተሳትፎ የበለጠ ለማሳደግ የአሰራር ማሻሻያዎች እየተደረጉ መሆኑን አምባሳደር ፍጹም ተናግረዋል። አሰራርን ከማዘመን አንጻር የኦንላይን ቪዛ አገልግሎት፣ ውክልና እና ሰነድ ማረጋገጥን በሚመለከት የሚወስደውን ረዥም ጊዜ በማሳጠር በ24 ሰዓት ማረጋገጥ የሚቻልበት ስርዓት ተዘርግቷል ብለዋል። የምክር ቤት አባላት ወደ ምርጫ ክልላቸው በሚሄዱበት ወቅት የዳያስፖራ ጉዳይ የሚስተናገድበትንና በስራ ላይ የሚገኙ ፕሮጀክቶችን ሂደት ክትትል እንዲያጠናክሩ ጠይቀዋል። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዮት ዋና ዳሬክተር ጃፋር በድሩ እንደተናገሩት የውጭ ግንኙነት ስራ በዲፕሎማቶች ብቻ የሚሰራ ባለመሆኑ የባለድርሻ አካላትን ሚና ለማሳደግ እየተሰራ ይገኛል። በውይይቱ የተሳተፉ የቋሚ ኮሚቴ ሃላፊዎች በበኩላቸው፥ ዳያስፖራው በኢንቨስትመንትና ሌሎች የልማት ስራዎች በሚያደርገው ተሳትፎ የሚያጋጥሙ የአሰራር ማነቆዎችን ለመፍታት ክትትልና ቁጥጥራቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ አረጋግጠዋል። በኢትዮጵያ ባለፉት ዓመታት ዳያስፖራው በሀገራዊ ዕድገት ውስጥ ተጠቃሚ እንዲሆን የተሰጠው ትኩረትና የተደረጉ የህግ ማሻሻያዎች ለውጥ እያመጡ ነው ብለዋል። በመድረኩ በዳያስፖራና ኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ እንዲሁም ፍልሰት አስተዳደር ላይ ትኩረት ያደረጉ ጽሁፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል። የምክክሩ ዓላማ የምክር ቤት አባላት በክረምት የእረፍት ጊዜ ወደ ምርጫ ክልላቸው በሚሄዱበት ወቅት በዳያስፖራ ዙሪያ መነሳት ያለባቸው ጉዳዮችና ከሀገር ውጭ ለስራ በሚሄዱበት ወቅትም ትኩረት ማድረግ ያለባቸውና የሚያስፈልጉ ድጋፎች ላይ የጋራ መግባባት ለመፍጠር መሆኑ ታውቋል።
በአማራ ክልል የተለያዩ ከተሞች ሰላምን የሚደግፍና ፅንፈኝነትን የሚያወግዝ ህዝባዊ ሰልፍ እየተካሄደ ነው
Jun 29, 2025 189
ባህርዳር ፤ሰኔ 22/2017(ኢዜአ)፦በአማራ ክልል የተለያዩ ከተሞች ሰላምና ልማትን የሚደግፍና ፅንፈኝነትን የሚያወግዝ ህዝባዊ ሰላማዊ ሰልፍ እየተካሄደ ነው። በሰላማዊ ሰልፉም የመንግስትን የልማትና የሰላም ጥረት በማድነቅ የተጠናከረ እገዛና ድጋፍ እናደርጋለን ሲሉ ተሳታፊዎቹ አረጋግጠዋል። በክልሉ አንዳንድ አካባቢዎች ፅንፈኛው ቡድን በዜጎች ላይ የሚፈፅመውን እገታ ግድያና ዘረፋ እናወግዛለን በማለት በሰልፉ ላይ ሃሳባቸውን እየገለፁም ይገኛሉ። የሰልፉ ተሳታፊዎች ሰላም እንፈልጋለን፣መንግስት ህግ በማስከበር የንጹሐንን ገዳዮች ለህግ ያቅርብልን፣ የልማት አርበኝነትን ለልጆቻችን እናወርሳለን፣ ሰላም የጋራ ሃብት ነው በጋራ ይለማል በጋራ ይጠበቃል፣ ሰላም ለሁሉም ሁሉም ለሰላም የሚሉና ሌሎችንም መልዕክቶች እያሰሙ ይገኛሉ።
በአማራ ክልል የመንግስትን የሰላም ጥሪ የተቀበሉ የቀድሞ ታጣቂዎች የተሀድሶ ስልጠና ወስደው ወደ ልማት እየተመለሱ ነው
Jun 28, 2025 147
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 21/2017(ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል የመንግስትን የሰላም ጥሪ የተቀበሉ የቀድሞ ታጣቂዎች የተሀድሶ ስልጠና ወስደው ወደ ልማት እንዲመለሱ እየተደረገ መሆኑን የአማራ ክልል የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ እሸቴ የሱፍ(ዶ/ር) ገለጹ። የቢሮ ኃላፊው ለኢዜአ እንደገለጹት፤ መንግስት ሁልጊዜ ለሰላም አማራጭ ቅድሚያ ይሰጣል። በክልሉ በጫካ ያሉ የታጠቁ አካላት የሰላም አማራጭን ተቀብለው ለሰላምና ለልማት እንዲሰሩ ተደጋጋሚ ጥሪ መደረጉን ገልጸዋል። በዚህም ባለፉት ወራት በርካታ የቀድሞ ታጣቂዎች የሰላም ጥሪውን ተቀብለው የተሃድሶ ስልጠና በመውሰድ መደበኛ ህይወታቸውን መምራት መጀመራቸውን ጠቅሰዋል። በአሁኑ ወቅትም የሰላም ጥሪውን ተቀብለው ለመጡ 12ሺህ የቀድሞ ታጣቂዎች የተሀድሶ ስልጠና ለመስጠትና ወደ ማህበረሰቡ ለመቀላቀል ዝግጅት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል። ቀደም ብሎ የክልሉ መንግስት በከተሞችና ቀበሌዎች ባካሄደው ህዝባዊ የምክክር መድረክ ህዝቡ ለሰላም አማራጭ ጽኑ ፍላጎት እንዳለው ማረጋገጫ መስጠቱን አንስተዋል። የሰላም አማራጭን በመግፋት የክልሉን ህዝብ በግጭት እንዲቆይ በሚያደርጉ ታጣቂዎች ላይ መንግስት የሚወስደውን ህግ የማስከበር እርምጃ ለማገዝ ሕዝቡ በቁርጠኝነት መቆሙንም ተናግረዋል። የጽንፈኛ ኃይሉ ቀሪ ታጣቂዎችም በግጭት የሚፈታ አንዳች ጥያቄ አለመኖሩን በመገንዘብ መንግስትና ህዝብ የሰጣቸውን የሰላም አማራጭ እንዲጠቀሙበት መልዕክት አስተላልፈዋል። የመንግስትን የሰላም ጥሪ የተቀበሉ የቀድሞ ታጣቂዎችን የተሀድሶ ስልጠና በመስጠትና ድጋፍ በማድረግ መደበኛ ህይወታቸውን እንዲመሩ እየተደረገ እንደሚገኝም ገልጸዋል። በመገባደድ ላይ ባለው በጀት ዓመት ያለፉት ወራትም የመንግስትን የሰላም ጥሪ የተቀበሉ 10ሺህ የቀድሞ ታጣቂዎች ከስህተታቸው በመማር መደበኛና ሰላማዊ ሕይወት የሚመሩበት ዕድል እንደተፈጠረላቸው አብራርተዋል። በተሳሳተ ስሌት ወደ ግጭት የገቡ የፅንፈኛ ቡድኑ አባላት ከስህተታቸው ትምህርት በመውሰድ መንግስት ያቀረበውን የሰላም አማራጭ እየተቀበሉ እንደሚገኙም አስረድተዋል። የሃይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎችና የክልሉ ህዝብ የታጣቂ ቡድኑ አባላት አለን የሚሉትን ጥያቄ በሰላማዊ መንገድ ማቅረብ እንዲችሉ ከፍተኛ እገዛ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል። በአሁኑ ወቅት የታጣቂ ኃይሉን የመረጃና የፋይናንስ ምንጭ በመበጣጠስ ህግና ሥርዓት የማስከበር ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል። የክልሉ የጸጥታ መዋቅርና የሠራዊት አባላትም ህብረተሰቡን በማሳተፍ የክልሉን ሰላምና ደህንነት የማስጠበቅ አቅም መፍጠራቸውን ገልጸዋል።
ወጣቶች ሰላምን በማዝለቅ ለጠንካራ ሃገረ መንግስት ግንባታ እየተወጡ ያለውን ሚና ሊያጠናክሩ ይገባል
Jun 28, 2025 120
ባህር ዳር፤ ሰኔ 21/2017 (ኢዜአ) ፡-ወጣቶች ሰላምን በማዝለቅ ለጠንካራ ሃገረ መንግስት ግንባታ እየተወጡ ያለውን ሚና አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ ተጠቆመ። በብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል የወጣቶች ክንፍ ከሰላም ሚኒስቴር ጋር በመተባበር "ሀገሬን እገነባለሁ ኃላፊነቴን እወጣለሁ" በሚል መሪ ሃሳብ ክልላዊ የውይይት መድረክ በባህር ዳር እየተካሄደ ነው። በብልጽግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የአደረጃጀት ዘርፍ ኃላፊ አቶ ፍስሃ ደሳለኝ በመድረኩ ላይ ባስተላለፉት መልእክት እንዳሉት ወጣቶች ለዘላቂ ሰላም ግንባታ የማይተካ ሚና አላቸው። በፅንፈኛ ኃይሉ ያጋጠሙ ተግዳሮቶችን በወጣቶችና ሌላው ማህበረሰብ የነቃ ተሳትፎ አሁን ላይ የክልሉ የሰላም ሁኔታ እየተሻሻለ መምጣቱን ገልጸዋል። ወጣቱ በመጣው ሰላም ላይ በመመስረትም የለውጡ ትሩፋት በሆነው የልማት ተግባራት ላይ ንቁ ተሳታፊ በመሆን የኢትዮጵያን ብልፅግና ለማረጋገጥ የሚጠበቅበትን እንዲወጣ አሳስበዋል። "ወጣትነት የእውቀትና የትኩስ ጉልበት ሃብት ነው" ያሉት አቶ ፍስሃ አሁን የተገኘውን ሰላም በማጽናት ለአገር እድገትና ለህዝብ ተጠቃሚነት መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል። አሰባሳቢ ትርክትን በማስረፅና ህብረ-ብሄራዊ አንድነትን በማጠናከር የኢትዮጵያን የብልፅግና ጉዞን ለማረጋገጥ ወጣቶች ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ሊረባረቡ እንደሚገባም አስገንዝበዋል። ሰላም የሁሉም ነገር መሰረት በመሆኑ በሰላም ግንባታ ላይ ወጣቶች የጀመሩትን ጥረት በቀጣይም አጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል ብለዋል። እንዲሁም የክረምት በጎ ፈቃድ አገልግሎት በውጤታማነት እንዲከናወን በተሳትፎና በማስተባበር ሚናቸውን እንዲወጡም አሳስበዋል። ለግጭት መንስኤ የሆኑ ችግሮች እንዲፈቱና ተከስተው ሲገኙም ፈጥኖ ግጭቶችን ለማስቆም የሚያስችሉ ስራዎች እየተሰሩ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በሰላም ሚኒስቴር የግጭት ጥናትና ትንተና ዴስክ ኃላፊ አቶ ይትባረክ ተስፋዬ ናቸው። የዛሬው መድረክም ወጣቶች በሰላምና በሀገረ መንግስት ግንባታ ላይ የራሳቸውን ድርሻ እንዲወጡ ግንዛቤ ለመፍጠር አልሞ የተዘጋጀ መሆኑን ተናግረዋል። በብልፅግና ፓርቲ የአማራ ክልል ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤት የዴሞክራሲና ባህል ግንባታ ዘርፍ ኃላፊ መስፍን አበጀ (ዶ/ር) በበኩላቸው ሀገራዊ ጥቅምን የሚያስጠብቅ ትውልድን ለመቅረፅና ለመገንባት የብልፅግና ፓርቲ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሚገኝ ገልፀዋል። በተለይ የተዛቡ አስተሳሰቦችን በማረም፣ ህብረ-ብሄራዊ አንድነትንና ዘላቂ ሰላምን ለማጠናከርና ልማትን ለማፋጠን ወጣቱ የጀመረውን ጥረት አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል። ‘‘ወጣቶች የሀገራችንን ሰላም አፅንተን ለማዝለቅና ልማቱን አጠናክረን ለማስቀጠል የዚህ ዘመን አሻጋሪ ትውልዶች ነን’’ ያለው ደግሞ የመድረኩ ተሳታፊ ወጣት ነቢዩ ጌቱ ነው። እኛ ወጣቶች የማንም ሃሳብ ተሸካሚና መጠቀሚያ ሳንሆን ሰላምን ከማፅናት ጎን ለጎን የስራ ባህላችንን በመለወጥ ወደ ብልፅግና የሚደረገውን ጉዞ አጠናክረን ልንቀጥል ይገባል ብሏል። ለአንድ ቀን በተዘጋጀው ክልላዊ የማጠናቀቂያ የወጣቶች መድረክ ላይም ከክልሉ ሁሉም አካባቢዎች የተውጣጡ ወጣቶች፣ የአማራ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ፅህፈት ኃላፊዎችና ሌሎች እንግዶች ተሳትፈዋል።
በኦሮሚያ ክልል የተገኘውን ሰላም በዘላቂነት ለማስቀጠል ህዝብን ያሳተፈ የተቀናጀ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል
Jun 27, 2025 227
አምቦ፣ ሰኔ 20/2017(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል የተገኘውን ሰላም በዘላቂነት ለማስቀጠል ህዝብን ያሳተፈ የተቀናጀ ስራ ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን የክልሉ ሚሊሻ ጽህፈት ቤት አስታወቀ። የክልሉ ሚሊሻ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ አበራ ቡኖ በተገኙበት በምዕራብ ሸዋ ዞን ቶኬ ኩታዬ ወረዳ የተሃድሶ ስልጠና የወሰዱ የሚሊሻ አመራሮች የምረቃ መርሃ ግብር ተካሄዷል። ኃላፊው በወቅቱ እንደገለጹት በክልሉ የተገኘውን ሰላም በዘላቂነት ለማጽናት ከህዝቡ ጋር በቅርበትና በቅንጅት እየተሰራ ነው። በሂደቱም ከህዝቡ ጋር የሰላምና ጸጥታ ስራዎችን የሚያስጠብቅ ጠንካራ የሚሊሻ አደረጃጀት በመፍጠር እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው በዚህም የሚፈለገው ውጤት እየተገኘ ነው ብለዋል። በቀጣይም በሁሉም አካባቢዎች ሰላምን የማስጠበቅና ጸጥታን የማስፈን ስራ በልዩ ትኩረት የሚሰራ መሆኑን አረጋግጠው የሚሊሻ አመራሮችና አባላትም ሃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ አሳስበዋል። የምዕራብ ሸዋ ዞን አስተዳዳሪ አቶ ዲዳ ጉደታ በበኩላቸው በዞኑ አስተማማኝ ሰላም በመስፈኑ ህዝቡ በተሟላ መልኩ የልማት ስራውን በማከናወን ላይ መሆኑን አንስተዋል። ከጥቂት ዓመታት በፊት በዞኑ ይስተዋል የነበረው የጸጥታ ችግር በአስተማማኝ መልኩ መፈታቱን ገልጸው በተጠናከረ መልኩ ቀጣይነት እንዲኖረው በቅንጅት ይሰራል ሲሉ ተናግረዋል። በዞኑ በሚገኙ ሁሉም ቀበሌዎች የአካባቢ ሰላምና ጸጥታ የሚጠብቁ የሚሊሻ አባላት የአካባቢያቸውን ሰላም ለመጠበቅ ይበልጥ መዘጋጀት እንዳለባቸው አስገንዝበዋል። ከተመራቂዎቹ መካከል ከባኮ ከተማ የሰለጠኑ አቶ አብዱ ኡመር፣ በስልጠና ቆይታቸው በቂ እውቀትና ክህሎት ማግኘታቸውን ገልጸው ባገኙት ስልጠና መሰረትም የሰላምና ጸጥታ ጥበቃ ስራቸውን እንደሚያጠናክሩ ገልጸዋል። ወደ ባኮ ከተማ ስመለስ ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በመሆን ህዝቡን ያሳተፈ የሰላምና ጸጥታ ጥበቃ ላይ በንቃት እሳተፋለሁ ብለዋል። ከወልመራ ወረዳ የመጡት አቶ ተሰማ ለገሰ፣ ከአካል ብቃት ጀምሮ ለሰላምና ጸጥታ ስራ አስፈላጊ የሆኑ ስልጠናዎችን ሲወስዱ መቆየታቸውን ገልጸዋል። ወደመጡበት አካባቢ ሲመለሱም ህዝቡን በማሳተፍ አስተማማኝ ሰለምና ጸጥታ በመገንባት ሂደት የላቀ ሚናቸውን ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን አረጋግጠዋል።
ኢትዮጵያ በአስደናቂ የህዳሴ ጉዞ ላይ ናት - የናይጄሪያ ምክትል ፕሬዝዳንት ካሺም ሼቲማ
Jun 27, 2025 169
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በአስደናቂ የህዳሴ ጉዞ ላይ ትገኛለች ሲሉ የናይጄሪያ ምክትል ፕሬዝዳንት ካሺም ሼቲማ ገለጹ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከናይጄሪያ ምክትል ፕሬዝዳንት ካሺም ሼቲማ ጋር ቁልፍ በሆኑ የሁለትዮሽ እና አህጉራዊ ጉዳዮች ላይ መወያየታቸው ይታወቃል። ምክትል ፕሬዝዳንቱ የኢትዮጵያን አስደናቂ ቅርሶችና ታሪኳን አጉልቶ በሚያሳይ መልኩ ታድሶ ለዕይታ ክፍት የሆነውን ብሔራዊ ቤተመንግሥትንም ጎብኝተዋል። ጉብኝታቸውን በተመለከተም በይፋዊ የክብር መዝገብ ላይ ባሰፈሩት የማስታወሻ መልዕክት ብሔራዊ ቤተ መንግሥቱ ህያው ታሪክ ነው ብለዋል። ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ቅኝ ያልተገዛች ብቸኛዋ ሀገር መሆኗን ያወሱት ምክትል ፕሬዝዳንቱ፥ በአስደናቂ የህዳሴ ጉዞ ላይ ትገኛለች ነው ያሉት። በኢትዮጵያ ድንቅ የታሪክ ጸጋና ታላቅ ሀገርነት ኩራት እንደተሰማቸውም ነው በመልዕክታቸው የጠቀሱት።
ሀገር በቀል የግጭት አፈታት ስርዓቶች ለዘላቂ ሰላም ግንባታ ስራ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው - ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ
Jun 27, 2025 163
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 20/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ሰላም ግንባታና በአብሮነት የመኖር እሴት እንዲጎለብት ሀገር በቀል የግጭት አፈታት ስርዓቶች ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ እንደሚገኙ የሰላም ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ ገለጹ። በተሳሳተ ስሌት ነፍጥ ያነገቡ አካላት መንግስት የፈጠረውን የሰላም አማራጭ እንዲቀበሉ በማስቻል በኩል የሀገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት አባቶች የማግባባት ሚናቸውን እየተወጡ እንደሚገኙ አስታውቀዋል። ሰላም ሚኒስቴር "ማህበራዊ ሀብቶቻችን ለህብረ-ብሔራዊ አንድነታችን" በሚል መሪ ሀሳብ ሀገር አቀፍ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የጎሳ መሪዎችና የሰላም ተቋማት አመራር አባላት የምክክር መድረክ አካሂዷል። የሰላም ሚኒስትር መሀመድ እድሪስ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያን ዘላቂ ሰላምና ደህንነት ለማረጋገጥ ሀገር በቀል የግጭት አፈታት ስርዓቶች የማይተካ ሚና አላቸው። መንግስት ኢትዮጵያ ካለፈችባቸው የፖለቲካ ታሪክ በሚመነጩ ተግዳሮቶች ለሚፈጠሩ የጸጥታ ችግሮች ምላሽ ለመስጠት የሰላም አማራጭን የማስፋትና ህግ የማስከበር ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። የሀገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት አባቶችም በተሳሳተ ስሌት ነፍጥ ያነገቡ አካላት መንግስት የፈጠረውን የሰላም አማራጭ እንዲቀበሉ በማስቻል ሂደት የማግባባት ሚናቸውን እየተወጡ እንደሚገኙ አንስተዋል። የሰላም ሚኒስቴርም የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ያካበቱትን የግጭት አፈታትና የሰላም ግንባታ ስራን ለማስቀጠል በትኩረት እየሰራ ነው ብለዋል። በአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ የተካሄደው የምክክር መድረክ የልምድ ልውውጥና የእርስ በእርስ ትውውቅ የተፈጠረበት መሆኑን ተናግረዋል። በተጨማሪም የመድረኩ ተሳታፊዎች በሀገር በቀል የሰላም ግንባታና የግጭት አፈታት ዕውቀትና እሴታቸውን በመጠቀም ቀጣይነት ያለው ስራ የሚሰሩበትን ሥርዓት መዘርጋቱን ገልጸዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከናይጄሪያ ምክትል ፕሬዚዳንት ጋር ተወያዩ
Jun 26, 2025 225
አዲስ አበባ፤ ሰኔ 19/2017(ኢዜአ)፦ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከናይጄሪያ ፌዴራላዊ ሪፐብሊክ ምክትል ፕሬዚዳንት ጋር ተወያይተዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት መረጃ ዛሬ ማምሻውን የናይጄሪያ ፌዴራላዊ ሪፐብሊክ ምክትል ፕሬዚዳንት ካሺም ሼቲማን ተቀብዬ ቁልፍ በሆኑ የሁለትዮሽ እና አህጉራዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይተናል ብለዋል።
ደቡብ ኮሪያ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዘመን ተሻጋሪ ወዳጅነት ወደላቀ የኢኮኖሚ ግንኙነት ማሳደግ ትሻለች
Jun 26, 2025 171
አዲስ አበባ፤ሰኔ 19/2017(ኢዜአ)፦ደቡብ ኮሪያ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ዘመን ተሻጋሪ ወዳጅነት ወደላቀ የኢንቨስትመንት እና ኢኮኖሚ ግንኙነት ማሳደግ እንደምትፈልግ የደቡብ ኮሪያ ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ጆ ሆ ያንግ ተናገሩ ፡፡ የኢፌድሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀ ስላሴ ከፍተኛ የደቡብ ኮሪያ ልዑካን ቡድን አባላትን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል፡፡ ውይይቱን አስመልክቶ ከኢዜአ ጋር ቆይታ ያደረጉት የደቡብ ኮሪያ ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባኤ ጆ ሆ ያንግ፥ ኢትዮጵያ ለደቡብ ኮሪያ ሰላም ለከፈለችው መስዋዕትነት ያላቸውን ክብር ለፕሬዝዳንት ታዬ መግለፃቸውን ተናግረዋል፡፡ ምክትል አፈ ጉባኤው አክለውም፥ ደቡብ ኮሪያ በኢንቨስትመንት እና ልማት ዘርፎች ከኢትዮጵያ ጋር በትብብር መስራት እንደምትፈልግ ተናግረዋል፡፡ ለዚህም በኢትዮጵያ መንግስት በኩል ቁርጠኝነቱ መኖሩን ከፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀ ስላሴ ማረጋገጫ ማግኘታቸውን ተናግረዋል፡፡ የልዑክ ቡድኑን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው ያነጋገሩት ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀ ስላሴ፥የሁለቱ ሀገራት ግንኙነት ወደ ላቀ ደረጃ እንዲሸጋገር በኢትዮጵያ በኩል ፍላጎት መኖሩን ተናግረዋል፡፡ የደቡብ ኮሪያ ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ያላቸው ኢንቨስትመንት እንዲጠናከር መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍም ያደርጋል። የደቡብ ኮሪያ የምክር ቤት አባላትን ያካተተው ከፍተኛ የልዑካን ቡድን በኢትዮጵያ ጉብኝት እያደረገም ይገኛል፡፡