ፖለቲካ
ህብረተሰቡ በግብይት ወቅት ሊያጋጥሙ የሚችሉ ህገወጥ ድርጊቶች ራሱን ሊከላከልና ሊጠብቅ እንደሚገባ ተመለከተ 
May 3, 2024 57
ሀዋሳ፣ ባህር ዳር ፣ ጋምቤላ ፤ ሚያዚያ 25/2016 (ኢዜአ) ፦ ህብረተሰቡ በዓልን ተከትሎ በግብይት ወቅት ሊያጋጥሙ የሚችሉ ህገወጥ ድርጊቶችን ሊከላከልና ራሱን ሊጠብቅ እንደሚገባ የሲዳማ፣ የአማራና ጋምቤላ ክልሎች ፖሊስ ኮሚሽኖች አስገነዘቡ። በየክልሎቹ ገበያ ስፍራ በግብይት ላይ የሀሰተኛ የብር ኖቶች ዝውውርና ምግብን ከባዕድ ነገሮች ጋር ቀላቅሎ የማቅረብ ወንጀሎች በበዓል ወቅት ከሚስተዋሉ ህገወጥ ድርጊቶች መካከል ዋናዎቹ መሆናቸው ነው የተጠቆመው። የሲዳማ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ሽመልስ ቶማስ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ህብረተሰቡ በበዓል ወቅት ግብይትን ተከትሎ ከሚያጋጥሙ ወንጀሎች ራሱን ሊከላከልና ሊጠብቅ ይገባል። በገበያ ስፍራ ህገ-ወጦች ሀሰተኛ የብር ኖቶችን ለግብይት ለመጠቀም የሚሞክሩ ስለሚኖሩ ህብረተሰቡ ጥንቃቄ እንዲያደርግ አሳስበዋል። በተጨማሪም ባዕድ ነገሮችን ከምግብ ጋር በመቀላቀል ለግብይት የሚያወጡ አካላትም ሊኖሩ ስለሚችሉ አስፈላጊውን ጥንቃቄ እንዲያደርግ ጠይቀዋል። ፖሊስ የወንጀል ድርጊቶቹን አስቀድሞ ለመከላከል ግንዛቤ የመፍጠርና የክትትልና ቁጥጥር ስራ እያከናወነ መሆኑን አስታውቀዋል። የአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን የሚዲያ ዋና ክፍል ኃላፊ ምክትል ኮማንደር መሳፍንት እሸቴ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ የትንሳኤ በዓል ህብረተሰቡ በደስታ ማሳለፍ እንዲችልና በሰላም እንዲያሳልፍ ፖሊስ አስፈላጊውን ሁሉ ዝግጅት አድርጓል።   ህብረተሳቡ በዓሉ በሰላም እንዲያሳልፍ በየደረጃው የሚገኘው የፀጥታ መዋቅር ከህብረተሰቡ ጋር በመቀናጀት የተሰጠውን ተልዕኮና ስምሪት በአግባቡ እየተወጣ እንደሚገኝ አመልክተዋል። በተለይ ህብረተሰቡ በግብይት ወቅት ከሚፈጸሙ ህገ ወጥ ድርጊቶች ራሱን እንዲጠብቅኝ አመልክተዋል። በተለይም ከሀሰተኛ የብር ኖቶች ልውውጥ ሊያጋጥም ስለሚችል በጥንቃቄ በመመልከት ግብይቱን እንዲፈጽሙ አሳስበዋል። በጋምቤላ ክልል ከመጪው የትንሳኤ በዓል ጋር ተያይዞ ህገ ወጥ ድርጊቶች እንዳይፈጸሙ አስፈላጊውን የክትትልና ቁጥጥር ስራ እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታውቋል።   ኮሚሽነር ኡሞድ ኡሞድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ከትንሳኤ በዓል ጋር ተያይዞ በግብይት ወቅት የስርቆትና ሌሎች ወንጀሎች እንዳይፈጸም ክትትልና ቁጥጥር እየተደረገ ነው። ህብረተሰቡም ከአላስፈላጊ ወንጀሎችና ህገወጥ ተግባራት ራሱን በመጠበቅ ድርጊቱን እንዲከላከል አሳስበዋል።  
በሀረሪ ክልል ሰላምና የህግ የበላይነትን ከማረጋገጥ አንፃር አበረታች ስራዎች ተሰርተዋል- የክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ
May 3, 2024 53
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 25/2016(ኢዜአ)፡- በሀረሪ ክልል ሰላምና የህግ የበላይነትን ከማረጋገጥ አንፃር አበረታች ስራዎች መሰራታቸውን የክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ገለጸ። የክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ቶፊቅ መሀመድ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በቢሮው በተከናወኑ ስራዎች ዙሪያ በሰጡት መግለጫ በክልሉ በተሰሩ ዘርፈ ብዙ ስራዎች ሰላምን ማስቀጠል ተችሏል። በተለይም ህዝቡን በማሳተፍና የሰላሙ ባላቤት በማድረግ በተሰራው ስራ ጉልህ ሚና አበርክቷል ብለዋል። የክልሉ ፖሊስ የሰው ሀይሉን በማሳደግ በስነ-ምግባር የታነፀ፣ በእውቀት የበለፀገ እንዲሆን ከማስቻል አንጻር በርካታ የፖሊስ አባላትን በማሰልጠን ወደ ስራ ማሰማራት መቻሉን ጠቁመዋል። በአንዳንድ የትራፊክ ፖሊስ አባላት ላይ የሚታየውን ብልሹ አሰራር ለመቅረፍና የቁጥጥር ስርዓቱን ለማጠናከር አዳዲስ የትራፊክ ፖሊስ አባላትን በማሰልጠን ወደ ስራ እንዲገቡ መደረጉን ገልጸዋል። ከዚህ በተጨማሪ በተለያዩ ጊዜ ከማህበረሰቡ የሚነሱትን ቅሬታዎች መሰረት በማድረግ የፀጥታ መዋቅር የማጥራት ስራዎች ሲሰሩ መቆየቱን የገለጹት ኃላፊው በዚህም ከስራ እንዲሰናበቱ የተደረጉ የፖሊስ አባሎች መኖራቸውን ጠቅሰዋል። እንዲሁም ቀድሞ በትራፊክ ቁጥጥር ላይ ይሰሩ የነበሩ 34 አባላት በተነሳባቸው ቅሬታ ምክንያት ከትራፊክ ቁጥጥር ስራ በማንሳት በሌሎች ክፍሎች እንዲመደቡ ተደርጓል ብለዋል። ሚሊሺያ ኃይሉን ከማጥራት አንፃርም 69 የሚሆኑ የሚሊሻያ አባላት በፈፀሙት ጥፋት እንዲሰናበቱ መደረጉን ገልጸዋል። የሰላም አረደጃጀቶች የማደራጀት ስራ መሰራቱን ገልጸው በአደረጃጀቶቹ አማካይነትም 4ሺህ 982 የሚሆኑ ቀላል ግጭቶችን በእርቅ እንዲፈቱ ማድረግ ተችሏል ብለዋል። ህገ-ወጥ ንግድን ለመከላከል በተሰራው ስራ ከ98 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የኮንትሮባንድ እቃዎች መያዛቸውንም ገልጸዋል። ከአጎራባች የምስራቅ ሐረርጌ ዞንና ማያ ከተማ እንዲሁም በክልሉ ከሚገኙ የፌደራል የፀጥታ ሀይላት ጋር በመቀናጀት የፀረ ሰላም እንቅስቃሴን የማክሸፍ ስራ ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት መሰራቱን ጠቁመው ህገወጥ የጦር መሳሪያዎችን ለመቆጣጠር በተከናወኑ ስራዎች የተለያዩ መሳሪያዎች በቁጥጥር ስር ማዋል መቻሉን ተናግረዋል። የበጀት ዓመቱ ቀሪዎቹ ወራት የክልሉን ሰላም ለማጎልበት የጸጥታ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ መግለጻቸውን የክልሉ ኮሙኒኬሽን ጽህፈት ቤት መረጃ ያመለክታል።
የኢትዮጵያ እና የኢራቅ ረዥም ዘመናት ያስቆጠረን የሁለትዮሽና ዘርፈ ብዙ ግንኙነት  ለማጠናከር ይሰራል 
May 2, 2024 119
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2016(ኢዜአ)፡-የኢትዮጵያ እና የኢራቅ ረዥም ዘመናት ያስቆጠረን የሁለትዮሽና ዘርፈ ብዙ ግንኙነትን ለማጠናከር እንደሚሰሩ በኢራቅ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሰኢድ ሙሁመድ ጅብሪል ገለጹ ። በኢፌዴሪ ልዩ መልዕክተኛ እና ባለሙሉሥልጣን አምባሳደር ሰኢድ ሙሁመድ ጅብሪል (ዶ/ር) በባግዳድ በሚገኘው ሰላም ቤተ መንግሥት በተካሔደው ሥነ-ሥርዓት ላይ በመገኘት የሹመት ደብዳቤያቸውን ለኢራቅ ሪፐብሊክ ፕሬዝዳንት አብዱላጢፍ ጀማል ረሽድ (ዶ/ር) አቅርበዋል። አምባሳደሩ በወቅቱ እንዳሉት በኢትዮጵያ እና ኢራቅ ረዥም ዘመናት ያስቆጠረውን የሁለትዮሽና ዘርፈ ብዙ ግንኙነት በፖለቲካ፣በኢኮኖሚ፣በኢነርጂ ፣ባህልና ቱሪዝም ዘርፍ ለማጠናከር ቁርጠኛ መሆናቸውን ገልጸዋል።   የኢራቅ መንግስት በድጋሜ በኢትዮጵያ ኤምባሲውን ለመክፈት ላደረገው ተነሳሽነት ምስጋና በማቅረብ የኢትዮጵያ መንግስት ጥያቄውን መቀበሉንና አስፈላጊውን እርዳታ ለማድረግ ያለውን ዝግጁነትም አብራርተዋል። አምባሳደሩ ፕሬዝዳንት ሳህለ-ወርቅ ዘውዴ ለኢራቁ ፕሬዝዳንት አብዱላጢፍ ጀማል ረሽድ(ዶ/ር) የላኩትን መልዕክትና የመልካም ምኞት አድርሰዋል። የኢራቁ ፕሬዝዳንት በበኩላቸው ኢራቅ ከኢትዮጵያ ጋር ያላት የሁለትዮሽ እና በባለብዙ ወገን ትብብር ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የኢራቅ መንግስት በኢትዮጵያ በድጋሜ ኤምባሲውን ለመክፈት አስፈላጊውን ዝግጅት ማጠናቀቁንና በኢትዮጵያም በኩል ተቀባይነትን ማግኘቱን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና ዕድገትን ለማረጋገጥ የጋራ ሀገራዊ ትርክቶች እንዲጎለብቱ እንሰራለን - ወጣት ምሁራን
May 2, 2024 90
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 24/2016(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና እድገትን ለማረጋገጥ የጋራ ሀገራዊ ገዢ ትርክቶች እንዲጎለብቱ ሙያዊ ኃላፊነታቸውን እንደሚወጡ ኢዜአ ያነጋገራቸው ወጣት ምሁራን ገለጹ። የተዛቡ ነጠላ ትርክቶች የኢትዮጵያውያን ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ መስተጋብር ላይ ችግር በመፍጠር፣ የታሰበው ሰላምና እድገት እንዳይረጋገጥ ስጋት ሲፈጥሩ ቆይተዋል። መንግስትም ለኢትዮጵያ ወደ ተሻለ ምዕራፍ መሻገር እንዲሁም ሀገራዊ አንድነትና ሰላምን ለማፅናት አሰባሳቢ የጋራ ትርክት መፍጠር ወሳኝ ነው በሚል አቋም እየሰራ ይገኛል። ኢዜአ ያነጋገራቸው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ወጣት ምሁራን በሀገሪቱ ተጨባጭ ሰላምን ለመገንባት፣ አብሮነትን ለማጠናከርና እድገትን ለማረጋገጥ አሰባሳቢ ትርክት መገንባት ወሳኝ እንደሆነ አንስተዋል። በሀረማያ ዩኒቨርሲቲ የህግ መምህር እንዳልካቸው አበራ ጠንካራ እና የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ወጣቶች አይተኬ ሚና እንዳላቸው ጠቅሷል። ጠንካራ ሀገረ መንግስት የመገንባት ሂደት አልተጠናቀቀም ያለው ወጣቱ ምሁር ከዚህ አኳያ ወጣቶች ትልቅ የቤት ስራ እንዳለባቸው ተናግሯል። በተለይም የህዝብን አንድነት ከሚሸረሽሩ ጉዳዮች በመራቅ ሁሉም በሀገሩ ጉዳይ በባለቤትነት እንዲሳተፍ እና ብሔራዊ መግባባት እንዲፈጠር መስራት አለብን ነው ያለው። በሰላሌ ዩኒቨርሲቲ የኢኮኖሚክስ መምህርቷ ቃልኪዳን ደረጄ በበኩሏ የሀገርን እድገት ወደ ኋላ የሚጎትቱ እና የህዝቡን አብሮነት የሚሸረሽሩ የፅንፈኝነት ትርክቶች መኖራቸውን ገልጻለች።   በመሆኑም ወጣት ምሁራን ህብረ ብሔራዊ አንድነትን የማጎልበት እና ትውልዱን በመልካም ሰብዕና የማነፅ ሙያዊ ኃላፊነት አለብን ነው ያለችው። ወጣቱ ትውልድ ሀገርንና ህዝብን አደጋ ላይ ከሚጥሉ ከፋፋይ አጀንዳዎች እና ከሀሰተኛ መረጃዎች መራቅ እንደሚገባው ያነሳው ደግሞ በሰመራ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች አገልግሎት ዲን አብዱ ሀንፍሬ ነው።   በአሁኑ ሰዓት ኢትዮጵያ እያጋጠሟት ካሉ ፈተናዎች እንድትወጣ የጋራ ሀገራዊ ትርክት መገንባት ወሳኝ እርምጃ መሆኑንም ነው ወጣት ምሁራኑ የገለጹት። ብሔራዊ መግባባት መፍጠር የሚያስችል ሀገራዊ ምክክር ለማድረግ መንግስት የጀመራቸው ስራዎች ለጋራ ገዥ ትርክት ግንባታ ትልቅ ዕድል እንደሚፈጥሩ አንስተዋል። መንግስት በሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ወጣቶችን ያሳተፉ ውይይቶችንና የግንዛቤ መድረኮችን በማስፋት ወጣቶች ስለ አሰባሳቢ ትርክቶች በአግባቡ እንዲረዱ የማድረግ ስራዎችን አጠናክሮ እንዲቀጥልም ጠይቀዋል።
የስቅለትና የትንሳዔ በዓላት በሰላም እንዲከበሩ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት አድርጎ ወደ ሥራ መግባቱን የጋራ ግብረ ኃይሉ አስታወቀ
May 2, 2024 105
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 24/2016(ኢዜአ)፡- የስቅለትና የፋሲካ በዓላት ያለምንም የፀጥታ ችግር በሰላም እንዲከበሩ ለማስቻል አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት አድርጎ ወደ ስራ መግባቱን የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል አስታወቀ፡፡ በክርስትና ዕምነት ተከታዮች ዘንድ በሃይማኖታዊ ሥነ-ሥርዓት ከሚከበሩ ታላላቅ ሐይማኖታዊ በዓላት መካከል አንዱና ዋነኛው የሆነው የ2016 ዓ.ም የስቅለትና የፋሲካ በዓላት በሰላም እንዲከበር ለማስቻል አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት አድርጎ ወደ ስራ መግባቱን የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል አስታውቋል፡፡ በዓላቱ በሰላም ተከብረው እንዲጠናቀቁ መላው የፀጥታ አካላቱን ያሳተፈ ውይይት ተከናውኗል፡፡   በመድረኩ ወቅታዊ የፀጥታ ሁኔታንና መደበኛ የወንጀል መከላከል የተግባር አፈፃፀሞች ላይ ትኩረት ያደረገ ገለፃ የተደረገ ሲሆን ከበዓላቱ መከበር ጋር ተያያዞ በከተማው ላይ እንደ ስጋት የሚታዩ ችግሮችን አስቀድሞ በመለየት በቀጣይ መከናወን በሚገባቸው ጉዳዮች ዙሪያ አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የወንጀል መከላከል ጠቅላይ መምሪያ ምክትል ኮሚሽነር ጀኔራል መላኩ ፈንታ በሰጡት መመሪያ በፅንፈኛ ቡድኖች ላይ እየተወሰደ ከሚገኘው ጠንካራ እርምጃ ጎን ለጎን የስቅለትና የፋሲካ በዓላት በሰላም እንዲከበሩ የፀጥታ አካላት ቅንጅታቸውን በማጠናከር የክፍለ ከተሞቻቸውን ተጨባጭና ነባራዊ ሁኔታ ያገናዘበ ፀጥታን የማረጋገጥ ተግባር ማከናወን ይጠበቅባቸዋል፡፡ ከዕለተ ስቅለቱ ጀምሮ የፋሲካ በዓልን ተከትሎ በሚመጡ የበዓል ሰሞን ሊኖር የሚችለው የሰውና የተሸከርካሪን እንቅስቃሴ ታሳቢ ያደረገ የወንጀልና የትራፊክ አደጋ ቅድመ መከላከል ተግባር ላይ ትኩረት እንደሚደረግ ምክትል ኮሚሽነሩ አስታውቀዋል፡፡   የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ሀላፊ ወይዘሮ ሊዲያ ግርማ በበኩላቸው በዓሉ በየቤቱ የሚከብር እንደመሆኑ መጠን እንቅስቃሴዎች ከበዓል በፊት ባሉ ቀናት እንደሚበዙ ጠቁመው በተለያዩ ቦታዎች በባዛሮች፤ በገበያ ቦታዎች ላይ በሚስተዋሉ የበዓል ግብዓቶች ላይ ሰው ሰራሽ የግብዓት እጥረትና የዋጋ ጭማሪ እንዳይደረግ የከተማ አስተዳደሩ ባቋቋመው ግብረ ሐይል ቁጥጥር እየተደረገ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡ ው በንግድ ስርዓቱ ላይ ህገ-ወጥ ተግባር የሚፈፅሙ ግለሰቦችን ለመቆጣጠር የሚደረገውን ተግባር በማገዝ ህብረተሰቡ መረጃ በመስጠት ሊተባበር ይገባል ብለዋል፡፡ የምርት አቅርቦት ላይ እና የቁም ከብት ገበያ ላይ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ እንዲኖር የሚያደርጉ ህገ-ወጥ ደላሎች ላይ ተገቢው ክትትል በማድረግ መቆጣጠር እንደሚገባም ጨምረው መግለጻቸውን የፌዴራል ፖሊስ መረጃ ያመላክታል፡፡ በተጨማሪም ባልተፈቀዱ ቦታዎች ላይ የሚደረግ ግብይትን መቆጣጠር ትኩረት እንደሚሰጠው ያብራሩት ሐላፊዋ ለትራፊክ ስጋት የሆነውን የጎዳና ላይ ንግድን ጨምሮ የስርቆት ወንጀል፤ ሀሰተኛ የብር ኖት ዝውውር፤ በምግብ ውስጥ ባዕድ ነገር ቀላቅለው በሚሸጡ አካላት ላይ ጠንካራ ቁጥጥር ማድረግና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በቅንጅት መስራት የትኩረት አቅጣጫዎች መሆናቸውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰላምና ፀጥታ ቢሮ ሐላፊ ወይዘሮ ሊዲያ ግርማ ገልፀዋል፡፡ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር ጌቱ አርጋው በዚህ ዓመት በርካታ ህዝባዊና ሐይማኖታዊ የአደባባይ በዓላት በሰላም መከበራቸውን አስታውሰው የ2016 ዓ.ም የስቅለትና የፋሲካ በዓላት በተመሳሳይ የፀጥታ ሁኔታ በሰላም እንዲያልፍ ቀደም ሲል የታዩ መልካም ተሞክሮዎችን በመቀመር ጥናት ላይ ያተኮረ የስምሪት አቅጣጫ ተግባራዊ እንደሚደረግ ገልፀው ከወቅታዊ የፀጥታ ሁኔታ አኳያ በከተማውዋና ዋና የገበያ ቦታዎች፤ በመዝናኛ አካባቢዎች፤ በቤተ እምነቶችና በጥናት በተለዩ አካባቢዎች ላይ ጠንካራ የጥበቃ ተግባር እንደሚከናወን አብራርተዋል፡፡ በተለይም የእምነቱ ተከታዮች በምሽት ወደ ቤተ እምነቶቹ ለአምልኮት ሲሄድ ምንም አይነት ስጋት እንዳይፈጠር ጠንካራ የጥበቃ ሥራ እንደሚከናወን ገልፀው ህብረተሰቡም ለሰላሙ ስጋት የሆኑ ነገሮች ሲያጋጥሙት ለፀጥታ አካላት ተገቢውን መረጃ በመስጠት ተባባሪ መሆን እንደሚጠበቅበት አሳስበዋል፡፡ ለመላው የክርስትና ዕምነት ተከታዮች በዓላቱ የጤና፣ የፍቅርና የመተሳሰብ እንዲሆን የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ኃይሉ መልካም ምኞቱን እየገለፀ ሊፈፀሙ የሚችሉ ወንጀሎችንና ድንገተኛ አደጋዎችን ከመከላከል አንፃር ጥንቃቄ ከማድረግ ባሻገር አጠራጣሪ ሁኔታዎች ሲያጋጥሙ በስልክ ቁጥር 011-1-11-01-11 እና በነፃ የስልክ መስመር 991 በመጠቀም ወይም በየአቅራቢያው ለሚገኙ የፀጥታ አካላት በአካል በመቅረብ ጥቆማና መረጃ መስጠት እንደሚቻል አስታውቋል፡፡
ለዘላቂ ሰላም ግንባታ ትኩረት በመስጠት ለመጪው ትውልድ የምትመች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ መረባረብ ይገባናል -የሰላም ሚኒስትር ብናልፍ አንዷለም
May 1, 2024 104
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2016(ኢዜአ)፡- ለዘላቂ ሰላም ግንባታ ትኩረት በመስጠት ለመጪው ትውልድ የምትመች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ በመረባረብ ይገባናል ሲሉ የሰላም ሚኒስትሩ ብናልፍ አንዷለም ገለጹ። ''ምክር ቤቶቻችን ለዘላቂ ሰላምና ለጠንካራ አገር ግንባታ ስኬታችን'' በሚል መሪ ሀሳብ የፌዴራልና የክልል ምክር ቤቶች የስልጠና እና የንቅናቄ መድረክ ተካሂዷል።   በሰላም ሚኒስቴር በተዘጋጀው በዚሁ መድረክ ላይ የህዝብ ተወካዮችና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች አባላት እንዲሁም የክልልና የከተማ መስተዳደር ምክር ቤቶች አፈ-ጉባኤዎች ታድመዋል። የሰላም ሚኒስትሩ ብናልፍ አንዷለም በዚሁ ጊዜ እንዳሉት በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና ብሄራዊ መግባባት በሚፈለገው ልክ መፍጠር ያልተቻለው ሁሉን ነገር ከትላንት ጋር ብቻ በማያያዝ ዛሬና ነገን በአግባቡ መመልከት ባለመቻሉ ነው። ለዘላቂ ሰላምና ለጠንካራ አገረ መንግስት ግንባታ ብሄራዊ መግባባት ወሳኝ ጉዳይ ቢሆንም ብሄራዊ መግባባትን ለመፍጠር የተኬደባቸው መንገዶች ትክክለኛ አቅጣጫን የተከተሉ እንዳልነበሩ ገልጸዋል። ይህም የምንመኘውንና የምንፈልገውን ብሄራዊ መግባባት መፍጠር እንዳንችል አድርጓል ነው ያሉት። ኢትዮጵያ የረጅም ጊዜ የመንግስት ምስረታ ታሪክ ያላትና ቀደምት የስልጣኔ ባለቤት መሆኗን አስታውሰው የቅርብ ጊዜ የምስረታ ታሪክ ያላቸውና በሁለንተናዊ ዕድገት ከኢትዮጵያ የቀደሙ አገሮች ዋነኛ ምስጢር ከትናንት ታሪካቸው ተምረው ነጋቸውን የሚያሳምር ስራ መስራት መሆኑን ገልጸዋል። ሁሉን ነገር ከትላንት ጋር ብቻ በማያያዝና ትላንት ላይ ተቸክሎ በመቆየት ለውጥ እንደማይመጣ ገልጸው ዛሬና ነገን በማሰብ በጋራ መትጋት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። ዘላቂ ሰላምና ብሄራዊ መግባባት ለመፍጠር ነገን መናፈቅና ለነገ የተሻለ መመኘት ወሳኝ መሆኑንም ነው ያብራሩት። ዛሬ ላይ በወሳኝ አገራዊ ጉዳዮች መግባባት በመፍጠር ነገ የምንመኛትን አገር እውን ማድረግ እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል። ለዚህም ዋልታ ረገጥ እሳቤዎችን በመተው የጋራ ትርክቶች ላይ በማተኮር ሀገራዊ መግባባት ለመፍጠር ሁላችንም በጋራ ልንሰራ ይገባል ብለዋል። ለዘላቂ ሰላም ግንባታ ትኩረት በመስጠት ለመጪው ትውልድ የምትመች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ መረባረብ እንደሚገባም ነው የተናገሩት። አገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ በዋና ዋና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በመነጋገር መግባባት ላይ ለመድረስ ያለው ሚና ከፍተኛ በመሆኑ ለኮሚሽኑ ውጤታማነት ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣም ጥሪ አቅርበዋል። የውይይቱ ተሳታፊዎች ኢትዮጵያዊያን በአብሮነትና በመከባበር ለትውልድ የሚሻገር መልካም ስራ መስራት ይገባናል ብለዋል። ኢትዮጵያ የብዝሃ ብሄሮች አገር እንደመሆኗ የሁሉንም ማንነት በእኩል ደረጃ መቀበል ለዘላቂ ሰላም ወሳኝ ነው ብለዋል። የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ፀሀይ ወራሳ እንደ አገር ያለውን ብዝሃነት ተቀብሎ የጋራ እሴቶች ላይ መስራትና የህዝቦችን አንድነት ማጠናከር ብሄራዊ መግባባት ለመፍጠር ቁልፍ መንገድ መሆኑን አንስተዋል። የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክር ቤት አፈ ጉባዔ ፋጤ ስርሞሎ በበኩላቸው በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምን ማስፈን የሁሉም ሃላፊነት ቢሆንም በተለይ አስፈጻሚ አካላት የሰላም ጉዳይ ላይ በትኩረት እንዲሰሩ የምክር ቤት አባላት የሚያደርጉትን ክትትልና ቁጥጥር ሊያጠናክሩ እንደሚገባም ነው ያነሱት።
ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ወጣት ምሁራን ሃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል
May 1, 2024 108
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 23/2016(ኢዜአ)፡- በኢትዮጵያ ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ወጣት ምሁራን ባላቸው እውቀት ሃላፊነታቸውን ሊወጡ እንደሚገባ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሃመድ ገለጹ። የብልጽግና ፓርቲ ወጣቶች ሊግ ”የምሁራን ወጣቶች ሚና ለሀገረ መንግስት ግንባታ” በሚል መሪ ሃሳብ ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር ሁለተኛ ዙር የፓናል ውይይት አካሂዷል።   በመድረኩ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሀመድ፣ ከሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች የተወጣጡ ወጣት ምሁራን እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል፡፡ የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሀመድ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት በኢትዮጵያ ምላሽ የሚሹ በርካታ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጥያቄዎች አሉ፡፡ ለነዚህ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተጀመረው ጥረት የወጣቶችን የላቀ ተሳትፎና ስራ የሚጠይቅ መሆኑን ተናግረዋል። መንግስት ጠንካራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት በርካታ ስራዎችን በማከናወን ላይ ቢገኝም አሁንም የወጣቶችን ተሳትፎ የሚጠይቁ ተግባራት መኖራቸውን አንስተዋል። ወጣቱ ትውልድ የነገ ሀገር ተረካቢ ብቻ ሳይሆን በሀገሪቱ ሁለንተናዊ የእድገት ጉዞ ውስጥ ቀዳሚ ባለቤት መሆኑን ገልጸዋል። በሀገሪቱ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ እና በሌሎች የልማት ዘርፎች የተገኙ አወንታዊ ለውጦች የወጣቶች አሻራ ያረፈባቸው እንደሆኑ ተናግረዋል። ኢትዮጵያ በርካታ አምራች ወጣት ሃይል ያላት መሆኗን በመጥቀስ አንዳንድ ልማቷንና ሰላሟን የማይፈልጉ አካላት ከጀርባ ሴራ ለመፈጸም እንደሚሰሩ ጠቁመዋል። ወጣቶች የዚህች ሀገር ባለቤት መሆናቸውን አውቀው በሀገረ መንግስት ግንባታ ላይ ያላቸውን ሚና በተገቢው መልኩ ሊወጡ ይገባል ሲሉ ሚኒስትሯ ተናግረዋል። በሀገሪቱ ጠንከራ ሀገረ መንግስት ለመገንባት የሚሰሩ ስራዎች ፍሬያማ እንዲሆኑ በምክንያታዊነት የሚያምን እና አለመግባባቶችን በንግግር መፍታት የሚችል ህብረተሰብ ማፍራት ወሳኝ መሆኑን ሚኒስትሯ ጠቅሰዋል። ለዚህም ደግሞ ምሁራን ወጣቶች ያላቸውን እውቀት እና ክህሎት በመጠቀም ለሀገረ መንግስት ግንባታው የሚረዱ ጥናታዊ ምርምሮችን በመስራት እና ህብረተሰቡን በማንቃት ትልቅ ሚና ሊጫወቱ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር ፈትሂ ማህዲ በበኩላቸው ወጣቶች በሀገሪቱ ኢኮኖሚያዊ እድገት ላይ ትልቅ ሚና በመጫወት ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል።   ለበርካታ ዘመናት ትውልዱ ስለ ሀገረ መንግስት ግንባታ ያለውን ግንዛቤ ለማጎልበት የሚያስችሉ በቂ ስራዎች አለመስራታቸው ሀገሪቷ ላይ ጫና ማሳደሩን ጠቁመዋል። ይህንንም ችግር ለመፍታት ወጣቱ ትውልድ በጠንካራ ሀገረ መንግስት ግንባታ ላይ የራሱን ሚና እንዲወጣ ማስቻል ይገባል ብለዋል። የብልጽግና ፓርቲ ወጣቶች ሊግ ምክትል ፕሬዝዳንት ወጣት ፈዲላ ቢያ በበኩሏ ሊጉ ከሁለት ወራት በፊት በጠንካራ ሀገረ መንግስት ግንባታ ሂደት የወጣት ምሁራንን ተሳትፎ ለማሳደግ በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ የፓናል ምክክር ማካሄዱን አስታውሳለች።   ይህን ተከትሎ የተካሄደው ሁለተኛው መድረክ በሀገሪቱ የሚገኙ ወጣቶች በሀገረ መንግስት ግንባታ ሂደት ውስጥ እያደረጉት ያለውን ሚና በመፈተሽ በቀጣይ የተሻለ ስራ ለመስራት የሚያስችል መሆኑን ገልጸዋል። በውይይቱ ላይ ከተሳተፉ ወጣት ምሁራን አንዱ የሆነው ወንድሙ ወዳጆ ወጣቶች ሀገሪቷ ከሚያጋጥሟት ፈተናዎች በመሻገር ጠንካራ ሀገረ መንግስት እንዲኖር የሚጠበቅብንን ሀገራዊ ግዴታ መወጣት አለብን ሲል ተናግሯል። ወጣት ጫልችሳ ምልኬቻ በበኩሉ ምሁራን ወጣቶች የሀገራችንን ችግሮች ለመፍታት የሚረዱና በእውቀትና ክህሎት ላይ የተመሰረቱ የመፍትሄ ሃሳቦች ማፍለቅ መቻል አለብን ብሏል፡፡
የማዕድን ዘርፍን በስትራቴጂ ለመምራት እየተሰራ ያለው ስራ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት - የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን
May 1, 2024 111
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 23 /2016(ኢዜአ)፦ የማዕድን ሚኒስቴር ዘርፍን በስትራቴጂ ለመምራት እየተሰራ ያለው ስራ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን አስታወቀ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የበጀት ዓመቱን የመንግሥት የስድስት ወራት የሥራ አፈጻጸም ሲገመግሙ የፌዴራል ሱፐርቪዥን ቡድን ተቋቁሞ ትኩረት በተሰጣቸው ዘርፎች ላይ የመስክ ምልከታ እንዲያደርግ አቅጣጫ ማስቀመጣቸው ይታወሳል። በዚህም የፕላንና ልማት ሚኒስቴር የሚያስተባብረው የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን የማዕድን ሚኒስቴር እና የተጠሪ ተቋማት ላብራቶሪን ጎብኝቷል። እንዲሁም በከበሩ ማዕድናት ላይ እሴት በመጨመር ለውጭ ገበያ የሚያቀርበውን ኦርቢት ኢትዮጵያ ፣ በከበሩ ማዕድናት ልየታ እና ደረጃ አወጣጥ ላይ ስልጠና የሚሰጠውን ዓለም አቀፍ የከበሩ ማዕድናት ፋውንዴሽን እና በደርባ ሚድሮክ ሲሚንቶ ፋብሪካ የመስክ ምልከታ አድርጓል። በዚሁ ወቅት በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በማዕድን ዘርፍ በተለይም በኦፓልና በከበሩ ማዕድናት የተከናወኑ ስራዎች፣ በግንባታ ላይ ያሉ የሲሚንቶ ፋብሪካዎች እና የነባር ፋብሪካዎች የምርት ሁኔታና የማዕድን ኢንዱስትሪ ግብዓት አቅርቦትን በሀገር ውስጥ ለመተካት የተሰሩ ስራዎች ቀርበዋል።   የፌዴራል ተቋማት ሱፐርቪዥን ቡድን አስተባባሪ ዶክተር ካሳሁን ተስፋዬ በዚሁ ወቅት ሚኒስቴሩ የዘርፉን ውጤታማነት ለማረጋገጥ የማዕድን ሴክተር ስትራቴጂ አዘጋጅቶ ወደ ስራ መግባቱ የሚበረታታ ነው ብለዋል። ወርቅ ፣ የከሰል ድንጋይና የከበሩ ማዕድናትን በተገቢው መንገድ ለመጠቀም በውስጥ አቅም የ5 አመት ስትራቴጂ ቀርፆ ወደ ስራ መግባቱን በጥንካሬ አንስተዋል። እንዲሁም ከስትራቴጂው የተቀዱ አምስት ኢንሼቲቮችን በፕሮጀክት ደረጃ በማዘጋጀት ወደ ስራ መገባቱ አበረታች ተግባር መሆኑን ጠቅሰዋል። የወርቅ የወጭ ንግድን ለማሳደግ እየተሰሩ ያሉ ስራዎች ለውጦችን በማስገኘት ላይ መሆናቸውን ተናግረዋል። በአንፃሩ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከያዘው ዓመታዊ እቅድ አንፃር አፈጻጸሙ አጥጋቢ እንዳልሆነ አንስተው የጎደለውን ለመሙላት በትኩረት መስራት እንደሚገባ አሳስበዋል። ባህላዊ የወርቅ አምራቾችን ወደ መካከለኛ አምራችነት ለማሳደግ እና የወርቅ አምራች ኩባንያዎችን ቁጥር ለመጨመር እየተሰራ ያለው ስራ አበረታች በመሆኑ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል። በወርቅ ላይ የሚታየውን የኮንትሮባንድ ንግድ ከፀጥታ አካላትና ከክልል አመራሮች ጋር በመቀናጀት መከላከል እንደሚገባ አመላክተዋል። ከውጭ የሚገባውን የድንጋይ ከሰል በሀገር ውስጥ ለመተካት እየተሰራ ያለው ስራ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ተናግረዋል። የከበሩ ማዕድናት ላይ እሴት ጨምሮ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ የተጀመሩ ስራዎች መጠናከር እንዳለባቸው ነው የተናገሩት ። በዘርፉ የተሰማሩ ኩባንያዎችን በፋይናንስ፣ በስልጠና እና አስፈላጊ በሆኑ ጉዳዮች መደገፍ ተገቢ መሆኑን ጠቅሰዋል። በግንባታ ላይ ያሉ የሲሚንቶ ፋብሪካዎች በተያዘላቸው ጊዜ እንዲጠናቀቁ በትኩረት መስራት እንደሚገባ በማሳሰብ በስራ ላይ ያሉ ፋብሪዎችን በመደገፍ በሙሉ አቅማቸው እንዲያመርቱ ማድረግ ይገባል ሲሉ አክለዋል። በተቋሙ ስር ያለውን ቤተ ሙከራ ዘመኑ በደረሰበት ቴክኖሎጂ ማደራጀት እንደሚገባ ዶክተር ካሳሁን ተናግረዋል። ተቋማዊ አደረጃጀት እና የስራ አካባቢን ምቹ በማድረግ ረገድ የተሰሩ ስራዎች ለሌሎች ተቋማት ተሞክሮ መሆን እንደሚችሉ ተናግረዋል።   የማዕድን ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሀብታሙ ተገኝ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት በማዕድን ዘርፍ ያሉትን ማነቆዎች ለማስወገድ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል። የማዕድን ሃብት ለሀገሪቱ ኢኮኖሚ ዕድገትና ለህብረተሰቡ ኑሮ መሻሻል ያለው አቅም ከፍተኛ ቢሆንም እያበረከተ ያለው ድርሻ ግን አነስተኛ መሆኑን ጠቁመዋል። ለዘርፉ በሚገባ አለማደግ በርካታ ውስጣዊና ውጫዊ ችግሮች እንዳሉ ያመለከቱት ሚኒስትሩ በተለይም ከዚህ ቀደም ዘርፉ የሚመራበት ስትራቴጂ አለመኖሩ ቀዳሚው ተግዳሮት እንደሆነ ተናግረዋል። መንግስት ሀገሪቱ ከማዕድን ተገቢውን ሃብት እንድታገኝ በሰጠው ልዩ ትኩረት በአስር አመት መሪ የልማት እቅድ ቅድሚያ ከተሰጠባቸው ጉዳዮች አንዱ መሆኑን አንስተዋል። ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የአምስት አመት የማዕድን ዘርፍ ስትራቴጂ በማዘጋጀት ወደ ስራ መግባቱን ተናግረዋል። እንዲሁም የማዕድን ምክር ቤት ተቋቁሙ ዘርፉን በተገቢውን መንገድ ለመምራት እየተሰራ እንደሚገኝ አስረድተዋል።
በፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ ሀላፊ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል ዘላለም መንግስቴ ከፍትሕ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ኤርሚያስ የማነ ብርሃን ጋር ተወያዩ
Apr 30, 2024 119
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22 /2016 (ኢዜአ)፦ በኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ ሀላፊ ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል ዘላለም መንግስቴ ከፍትሕ ሚኒስቴር የተቋም ግንባታ እና ሪፎርም ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ኤርሚያስ የማነ ብርሃን ጋር ተወያዩ። በኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ቢሮ በሰብዓዊ መብት አያያዝ ዙሪያ እና የወንጀል ምርመራን በቴክኖሎጂ ከማዘመን አንፃር የተሰሩ ስራዎችን ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል ዘላለም መንግስቴ ገለጻ ማድረጋቸው ተመላክቷል። ምክትል ኮሚሽነር ጀነራል ዘላለም መንግስቴ ለፍትህ ሚኒስትር ዴኤታው እና በዘርፉ ለሚገኙ ከፍተኛ አመራሮች ገለፃ አድርገዋል፡፡ ከገለፃው ጎን ለጎን የፍትሕ ሚኒስቴር የተቋም ግንባታ እና ሪፎርም ዘርፍ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ኤርሚያስ የማነ ብርሃን ከልዑክ ቡድናቸው ጋር በቢሮው የተሰሩ የሪፎርም ስራዎችን እና የወንጀል ምርመራን በቴክኖሎጂ ከማዘመን አንፃር የተሰሩ ስራዎችን ምልከታ አድርገዋል፡፡ አባላቱ በተመለከቷቸው የሪፎርም ስራዎች መደሰታቸውንና ለፍትህ ስርአቱ ተስፋ የሰነቀ ስራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በቀጣይም ሁለቱም ተቋማት በሪፎርም ስራዎች ዙሪያ በጋራ ለመስራት ከስምምነት ላይ መድረሳቸውን በፌደራል ፖሊስ የወንጀል ምርመራ ቢሮ መረጃ ያመለክታል፡፡
በአፍሪካ ዘላቂ ሰላም ልማትና ዴሞክራሲ ለማረጋገጥና ብቁ አመራር ለማፍራት በሚደረገው ጥረት የኢትዮጵያ ሚና ተጠናክሮ እንደቀጠለ ነው
Apr 30, 2024 112
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 22/2016(ኢዜአ)፦ በአፍሪካ ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና ዴሞክራሲን ለማረጋገጥና ብቁ አመራር ለማፍራት በሚደረገው ጥረት የኢትዮጵያ ሚና ተጠናክሮ መቀጠሉን የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት ዛዲግ አብርሃ ገለጹ። በአካዳሚው በሁለት ወራት ብቻ ከ120 በላይ የአፍሪካ አገራት አመራሮች ሥልጠና መውሰዳቸውንም ተናግረዋል። የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ተቀማጭነታቸውን በአዲስ አበባ ካደረጉ የተለያዩ የአፍሪካ አገራት አምባሳደሮችና ዲፕሎማቶች ጋር ውይይት አድርጓል። በመድረኩ ንግግር ያደረጉት የአፍሪካ አመራር ልህቀት አካዳሚ ፕሬዝዳንት ዛዲግ አብርሃ፤ አካዳሚው ከኢትዮጵያም ባለፈ በመላ አፍሪካ ብቁ መሪዎችን ለማፍራት እየሰራ መሆኑን ገልፀዋል።   በአፍሪካ ዘላቂ ሰላም፣ ልማትና ዴሞክራሲ ለማረጋገጥና ብቁ አመራር ለማፍራት በሚደረገው ጥረት የኢትዮጵያ ሚና ከጥንት እስካሁንም ተጠናክሮ መቀጠሉን ተናግረዋል። ኢትዮጵያ የቀድሞውን የኬንያ መሪ ጆሞ ኬንያታ እና የነፃነት ታጋዩን ኔልሰን ማንዴላ ማሰልጠኗን አስታውሰው፤ በዘመናዊ የአመራር ማሰልጠኛ በርካቶች እየሰለጠኑ መሆኑን ተናግረዋል። አካዳሚው የአፍሪካን ችግር የሚፈታ ብቁ አመራር ለማፍራት በሚያስችል መልኩ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሃሳብ አመንጪነት በዘመናዊ መልኩ የተደራጀ መሆኑንም ጠቅሰዋል። አሁን ላይ ሥልጠና ለመውሰድ ከፍተኛ ፍላጎት መኖሩን ገልጸው፤ ይህንን ፍላጎት ተግባራዊ ለማድረግም በትኩረት ይሰራል ብለዋል። አካዳሚው በአህጉሪቱ የተሰጠውን ተልዕኮ ለማሳካት የሚያስችሉ ሥራዎችን በስፋት እያከናወነ መሆኑን ተናግረው፤ ባለፉት ሁለት ወራት ብቻ ከ120 በላይ የአፍሪካ አገራት አመራሮች ሥልጠና መውሰዳቸውን ጠቅሰዋል። የመድረኩ ተሳታፊዎችም በተሟላና ዘመናዊ በሆነ መልኩ የተገነባው አካዳሚው ዓላማውም የሚደነቅ በመሆኑ የሁላችንም ድጋፍና እገዛ ያስፈልገዋል ብለዋል። በዚህ ረገድ ኢትዮጵያ እያደረገች ላለው የላቀ አስተዋጽዖ ምስጋናቸውን በማቅረብ ሌሎች አገራትም ይህንን መልካም አርዓያ ሊከተሉ ይገባል ብለዋል።    
ዘመናዊ ሰራዊት የመገንባት ሒደት በተከታታይ ስልጠና ተጠናክሮ ይቀጥላል- ሌተናል ጄኔራል ደስታ አብቼ
Apr 30, 2024 134
አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 22/2016(ኢዜአ)፦ ዘመናዊ ሰራዊት የመገንባት ሒደቱ በተከታታይ ስልጠና ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ ሃላፊ ሌተናል ጄኔራል ደስታ አብቼ ገልፀዋል። የውጊያ ምህንድስና ክፍለጦር ያሰለጠናቸውን የውጊያ ምህንድስና ሙያተኞች በዛሬው ዕለት አስመርቋል። በምረቃ መርሀ- ግብሩ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የመከላከያ መሐንዲስ ዋና መምሪያ ሃላፊ ሌተናል ጄኔራል ደስታ አብቼ ዘመናዊ ሰራዊት የመገንባት ሒደቱ በተከታታይ ስልጠና ተጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑንም ተናግረዋል።   የውጊያ ምህንድስና ክፍለጦር የውጊያ ድጋፍ የመስጠት ግዳጁን በአስተማማኝ እየተወጣ መሆኑን የተናገሩት ጄኔራል መኮንኑ በተለይም የታላቁ ህዳሴ ግድብ ግንባታን ለማደናቀፍ መዳረሻ መንገዶች ላይ ፀረ-ሰላም ኃይሎች የሚቀብሯቸውን ፈንጂና ተተኳሾች በማክሸፍ የውጊያ ምህንድስና ሙያተኞች ለሀገር ልማት በፅናት እየሰሩ ነው ብለዋል።   የውጊያ ምህንድስና ክፍለጦር አባላት አልሸባብ በሶማሌያ ድንበር አካባቢዎች የጥፋት ተልዕኮውን እንዳያሳካም ከሌሎች የሰራዊቱ ክፍሎች ጋር በመሆን በአስቸጋሪ የአየር ፀባይና የመሬት ገፆች ላይ የህይወት መስዋዕትነትም ጭምር በመክፈል ግዳጅ የተወጡ ጀግኖች መሆናቸውንም ገልፀዋል። ተመራቂዎቹ በመሰናክል አስቀማጭና አስወጋጅ መሠረታዊ ሙያ የተዋጊ መሐንዲስ እንዲሁም የተገጣጣሚ የተንቀሳቃሽና የተንሳፋፊ ድልድዮች የግዳጅ አፈፃፀም ሙሉ ዕውቀትና ብቃት እንዲይዙ የሚያስችል ሥልጠና የተሰጣቸው መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የውጊያ ምህንድስና ክፍለጦር ዋና አዛዥ ኮሎኔል ተስፋዬ ኩምሳ ናቸው።   በተቀመጠው የስልጠና መርሀ ግብር መሠረት በጠላት የሚጠመዱ የመስክ ወጥመዶችን ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ መሰናክሎችን ማስወገድ ለወገን ጦር ግዳጅ አፈፃፀም ምቹ ሁኔታን መፍጠር የጠላትን ግስጋሴ የመግታትና የወገንን እንቅስቃሴ የሚያቀላጥፉ ሥልጠናዎችን የወሰዱና ብቃታቸው በፈተና የተረጋገጠ መሆኑንም ኮሎኔል ተስፋዬ መናገራቸውን ከመከላከያ ሰራዊት የተገኘ ውመረጃ ያመለክታል። ተመራቂዎቹም በሠለጠኑት ሙያ ሀገራቸውን በታማኝነት ለማገልገል መዘጋጀታቸውን ገልፀዋል።
በኢትዮጵያ አሰባሳቢ የወል ትርክቶችን በመገንባት ረገድ የበኩላችንን ለመወጣት ተዘጋጅተናል
Apr 30, 2024 118
አዲስ አበባ ፤ ሚያዝያ 22/2016 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያን የቆዩ ስብራቶች በመጠገን አሰባሳቢና የወል ትርክቶችን በመገንባት ረገድ የበኩላችንን ለመወጣት ተዘጋጅተናል ሲሉ የኮሙኒኬሽን አመራሮችና ባለሙያዎች ገለጹ። በኢትዮጵያ ከስድስት አመታት በፊት የመጣውን ለውጥ ተከትሎ በመደመር እሳቤ ሁሉንም አሳታፊ ያደረገ የኢኮኖሚ፣ የማልማትና የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ሂደት ተጠናክሮ ቀጥሏል። በዋልታ ረገጥ እሳቤዎች ሲንከባለሉ የመጡትን የጥላቻና የመገፋፋት ትርክቶች በመቀየር የጋራና አሰባሳቢ ትርክቶችን የመገንባት ስራም በስፋት እየተከናወነ ይገኛል። በመሆኑም ሀገራዊ መግባባት በመፍጠር ለሁሉም የምትመችና የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ከምንም በላይ የጋራ ጥረትና ትብብር ማድረግ እንደሚገባ ይታመናል። በዚሁ ጉዳይ ላይ ኢዜአ ያነጋገራቸው የኮሙኒኬሽን አመራሮችና ባለሙያዎች፤ የኢትዮጵያን የቆዩ ስብራቶች በመጠገን አሰባሳቢና የወል ትርክቶችን በመገንባት ረገድ የበኩላችንን ድርሻ ለመወጣት ተዘጋጅተናል ሲሉ ተናግረዋል። የሀዋሳ ከተማ ኮሙኒኬሽን መምሪያ ሃላፊ ምርጫዬ ደመቀ፤ በኢትዮጵያ አሰባሳቢ ትርክትን የመገንባት ተግባር የሚዲያና ኮሙንኬሽን ተቀዳሚ ተግባር መሆኑን አንስተዋል። በመሆኑም በዋልታ ረገጥ እሳቤዎች ጥላቻና ቁርሾ የሚፈጥሩ ትርክቶችን በማረም የሚያቀራርቡ አሰባሳቢ ትርክቶችን ለማጉላት መስራት ይጠበቅብናል ብለዋል። ለዚህም የኮሙንኬሽን አመራርና ባለሙያዎች ከምንጊዜውም በላይ ዝግጁ በመሆን ወደ ስራ ገብተናል ሲሉ ተናግረዋል።   የስልጤ ዞን ኮሙኒኬሽን መምሪያ ኃላፊ ሳሊያ ሐሰን፤ በሀገር ጉዳይ ከሚያለያዩና ተቃርኖ ከሚያባብሱ ጉዳዮች በመራቅ ከምንም በላይ ለአብሮነትና አንድነት ለመስራት ተዘጋጅተናል ብለዋል። የሀገር አንድነትና ብሄራዊ መግባባት የሁሉም ነገር መሰረት መሆኑን ጠቅሰው ልዩነቶችን በመስበክ አብሮነትን መሸርሸር ለማንም የማይጠቅምና ሀገርንም የሚጎዳ መሆኑን ጠቅሰዋል።   የኮንታ ዞን የኮሙኒኬሽን ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አበበ ጎበና፤ በመደመር እሳቤ ሀገራዊ አንድነትን በማጎልበት ልማትና ብልጽግናን ለማረጋገጥ መስራት የሁላችንም ሃላፊነት ሊሆን ይገባል ብለዋል።    
ለሀገራዊ የምክክር ስኬት የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ  የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተናገሩ
Apr 30, 2024 125
አሶሳ/ሐረር ሚያዚያ 22/2016 (ኢዜአ)፡- ለሀገራዊ ምክክር ስኬት የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ አስተያየታቸውን ለኢዜአ የሰጡ የአሶሳና ሐረር ከተሞች የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ተናገሩ። አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡ የአሶሳ ከተማ ነዋሪዎች መካከል ወይዘሮ ሃሰንያ ሱሊማን እንዳሉት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልም ሆነ በሌሎች የሀገሪቱ አካባቢዎች በርካታ ፈተናዎች ሲያጋጥሙን ቆይተዋል፡፡ እነዚህ ፈተናዎች ለግጭት እንዲዳርጉን ባለመፍቀድ በሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን አማካኝነት በሚካሄድ ንግግር አጃንዳዎች ሆነው እንደሚመጡ መፍትሄም ያገኛሉ ብለው እንደሚያምኑ ተናግረዋል። "የምክክር ውጤት ሠላም ነው" የሚሉት ወይዘሮ ሃሰንያ፤ የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ ዓላማ ደግሞ ሠላምን ከማስፈን ባሻገር ወንድማማችነትን የበለጠ ስለሚያጠናክር የድርሻዬን ለመወጣት ዝግጁ ነኝ ብለዋል።   አቶ ሰለሞን ካሳ የተባሉ የከተማው ነዋሪ በበኩላቸው ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን የሚሠራው ለሀገር ሰላም እንደሆነ ይገልጻሉ። በውይይት የሚነሱ ሃሳቦች ችግሮቻችንን በመፍታት አንድነታችንን ያጠናክራሉ የሚሉት ነዋሪው ኮሚሽኑ ሀገራዊ ምክክር እንዲካሄድ እያደረገ የሚገኘው ጥረት ላይ የድርሻቸውን ለመወጣት እንደሚተጉ ተናግረዋል፡፡   ወይዘሮ አሙና አብዱልዋሂድ የተባሉ የአሶሳ ከተማ ነዋሪም የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ያልተግባባንባቸውን የሀገራችንን የውስጥ ጉዳዮች ሶስተኛ ወገን ሳይገባ በራሳችን መፍታት ያስችለናል ብለዋል። ይህ ደግሞ በሐሳብ የበላይነት በማመን እና ችግሮችን ተነጋግሮ በመፍታት ሀገራችንን በሠላማዊ እና በተረጋጋ መንገድ መምራት ያስችለናል ሲሉ አመልክተዋል፡፡ እንደ አንድ የሀገር ዜጋ እኛ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ነዋሪዎች የኮሚሽኑ ጥረት እንዲሳካ የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ ገልጸዋል። ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ ስኬታማ እንዲሆን ሁሉም የበኩሉን ድጋፍ ማድረግ ይገባዋል ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።   ሀገራዊ ምክክሩ የሚታዩ ችግሮችን በዘላቂነት ለመፍታት ተስፋ የሚሰጥና የሚበረታታ ነው ያሉት ደግሞ የሐረር ከተማ ነዋሪ መምህር ቶማስ ዱባለ ናቸው።   በምክክር ኮምሽኑ በሐረሪ ክልል የህብረተሰብ ተወካይ ሆነው ከተመረጡት መካከል አቶ መስፍን አክሊሉ ሀገራዊ ምክክሩ ጦርነትና ግጭቶችን የማስወገድና እንደ ሀገር የታሰበው ዘላቂ ሰላምና መረጋጋት እንዲያመጣ የሚያስችል ነው ብለዋል። በመሆኑም እንደ ማህበረሰብ ተወካይ ለሀገራዊ ምክክሩ ስኬት የሚጠበቅብኝን ለመወጣት ተዘጋጅቻለሁ ብለዋል። እንደ ነዋሪዎቹ ገለጻ የምክክሩ ሂደት ውጤታማነት የሚረጋገጠው ሁሉም በባለቤትነት ሲሳተፍ በመሆኑ ለዚህም የሚጠበቅብንን መወጣት ይገባል ብለዋል።              
የሚዲያ ተቋማቱ የሀገራዊ ምክክሩ ሂደት ስኬታማ እንዲሆን ሚናቸውን ማጎልበት እንደሚገባቸው ተጠቆመ
Apr 30, 2024 127
ሐረር ፤ ሚያዚያ 22/2016 (ኢዜአ)፡- የሚዲያ ተቋማት የሀገራዊ ምክክሩ ሂደት ስኬታማ እንዲሆን እየሰሯቸው ያሉትን ስራዎች ማጎልበት እንደሚገባቸው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ። የቋሚ ኮሚቴው አባላት የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን እና የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ሐረር ቅርንጫፍን እንዲሁም የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሐረሪ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤትን የስራ እንቅስቃሴ ተመልክተው ከተወካዮቻቸው ጋር ውይይት አካሂደዋል።   የቋሚ ኮሚቴው አባልና የሚዲያ ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ አቦኔ ዓለም እንዳመለከቱት፤ የምልከታው ዋና ዓላማ የተቋማቱን ቅርንጫፎች የሥራ አፈጻጸምና ለኅብረተሰቡ የሚሰጡትን አገልግሎት እንዲሁም እያጋጠማቸው ያለውን ተግዳሮት ለመለየትና ምክረ ሀሳብ ለማቅረብ ነው። የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን እና የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ሐረር ቅርንጫፍዎች በተወሰነ የሰው ሃይል ሰፊ አካባቢዎችን ለመሸፈን እየሰሩ መሆኑንና የተሻለ ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም በተግባር መመልከታቸውን ገልጸዋል። በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ሐረር ቅርንጫፍ ከምርጫ ማግስት ጀምሮ አዲስ አደረጃጀት በመዘርጋት ለዜጎች በምርጫና በሌሎች ግንዛቤን ከመፍጠር እንዲሁም ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር እያከናወኑ ያለው ስራ አበረታች መሆኑን በማውሳት። የሚዲያ ተቋማቱ በተለይም ለሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ ሂደት ስኬታማ እንዲሆን ግንዛቤን ከማጎልበት አንጻር የተሻለ ስራ ማከናወን ይገባቸዋል ብለዋል። እንዲሁም ሙስናና ብልሹ አሰራሮችን ከመታገል አንጻርም ቅርንጫፍ ፅህፈት ቤቶቹ እያከናወኑ የሚገኘውን ስራ ማጎልበት ይገባቸዋል ያሉት ወይዘሮ አቦኔ፤ በተለይም መድረኮችን ብቻ ተከትሎ መዘገብ ሳይሆን አቅደው መሥራት ይጠበቅባቸዋል ብለዋል። የቋሚ ኮሚቴ አባል እጅጉ መላኬ በበኩላቸው በክልሉ የሚገኙ የሚዲያ ተቋማት በህዝቦች መካከል በተለይም በሐረር አካባቢ ያለው መልካም እሴት እንዲጎለብትና የመልካም አስተዳደርና ብልሹ አሰራሮች እንዲቀረፉ የሚሰሯቸው ስራዎች አበረታች ነው ብለዋል።   የሚዲያ ተቋማቱ የጀመሩትን ቅንጅታዊ አሰራር አጠናክረው እንዲቀጥሉ አስገንዝበው በተለይም በቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶቹ እየታዩ የሚገኙ ተግዳሮቶችም የሚፈቱበት መንገድ መመቻቸት እንደሚገባ አሳስበዋል። ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቱ ባለፉት ዘጠኝ ወራት ካቀደው 85 በመቶ ስራ ማከናወኑን የገለጹት ደግሞ በኢትዮዽያ ምርጫ ቦርድ የሐረሪ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ጌታቸው ቦጋለ ናቸው።   በተለይም የቋሚ ኮሚቴ አባላቱ ያቀረቡትን ለትምህርት ቤቶች እና ለሁሉም ማህበረሰብ አካላት ግንዛቤ የመፍጠር ስራ ምክረ ሀሳብ እንደ ግብዓት በመውሰድ በቀጣይ የተሻለና ተከታታይነት ያለው ሥራ ይሰራል ብለዋል። የቋሚ ኮሚቴው አባላት ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቱ ድረስ በአካል ተገኝተው ያደረጉት ጉብኝት ለተቋሙ ትልቅ ግብዓት እንደሆነ የገለጹት ደግሞ በኢትዮዽያ ብሮድካስት ኮርፖሬሽን የሐረር ስቱዲዩ አስተባባሪ አቶ አብዱሰላም መሐመድ ናቸው።   በተለይም ተቋሙ ያለውን ውስን የሰው ሃይል በመጠቀም እቅድ አውጥቶ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው በቀጣይም ከቋሚ ኮሚቴው የተሰጠውን ገንቢ ግብረ መልስ በመጠቀም የተሻለ ስራ ለመስራት ዝግጅት መደረጉን ተናግረዋል።።    
በክልሉ ለህግ የበላይነት መከበር የፍትህ ስርዓቱን የበለጠ ማጠናከርና የህዝብ ተሳትፎን ማጎልበት ይገባል
Apr 30, 2024 116
ጎንደር፣ሚያዚያ 22/2016 ዓ/ም (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ለህግ የበላይነት መከበር የፍትህ ስርዓቱን የበለጠ ማጠናከርና የህዝብ ተሳትፎን ማጎልበት እንደሚገባ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወይዘሮ ፋንቱ ተስፋዬ ገለጹ፡፡ የአማራ ክልል የፍትህ ዘርፍ ትራንስፎርሜሽን ኮሚቴ በጎንደር ከተማ ያዘጋጀው ህዝባዊ የውይይት መድረክ ትናንት ተካሂዷል፡፡   አፈ ጉባኤዋ ወይዘሮ ፋንቱ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ የህግ የበላይነት መከበር ለሰላም፣ ለልማትና ዕድገት ፋይዳው የጎላ ነው። ለዚህም የህግ የበላይነት የበለጠ ለማጠናከር በሚያስችል መንገድ የፍትህ ስርዓቱ የሪፎርም ስራዎች ይከናወናሉ። በተለይም ለፍትህ ስርዓቱ መቃናት የህዝቡ አበርክቶ ወሳኝ መሆኑን ጠቅሰው፤ ህዝቡ ፍትህ የማግኘት መብቱ በተሟላ መንገድ እውን እንዲሆን የተጀመሩ የሪፎርም ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል፡፡ በክልል ደረጃ የፍትህ ትራንስፎርሜሽን ኮሚቴ ተዋቅሮ ወደ ስራ የገባ ሲሆን፤ ከመድረኩ የሚገኙ ግብዓቶችን በመጠቀም የፍትህ ስርዓቱ የህዝብን አመኔታና እርካታ በሚያረጋግጥ መልኩ ተልዕኮውን እንዲወጣ እንደሚደረግ ተናግረዋል። የክልሉ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት አቶ አብዬ ካሳሁን በበኩላቸው እንደተናገሩት፤ የክልሉ ፍርድ ቤቶች የሚያጋጥሙ ችግሮችን በመፍታት የህግ የበላይነት እንዲከበር የሚጠበቅባቸውን እየተወጡ ነው፡፡   የፍትህ አገልግሎት ተደራሽነትን ለማረጋገጥም በዋና ከተሞችና ወረዳዎች 220 የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቶችንና ቋሚ ምድብ ችሎቶችን በማቋቋም ለህብረተሰቡ የዳኝነት አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ የጎንደር ከተማ ከንቲባ ተወካይ አቶ ግርማይ ልጃለም በበኩላቸው፤ ከተማ አስተዳደሩ የህዝቡን የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመፍታት የከንቲባና የስራ አስኪያጅ ችሎቶችን አቋቁሞ እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።   የችሎቶቹ መቋቋም የፍርድ ቤቶችን የስራ ጫና በማቃለል ጉልህ ሚና እንዳላቸው ጠቅሰው፤ ይህም ለፍትህ ስርዓቱ መጠናከር ፋይዳቸው የጎላ እንደሆነም አመልክተዋል፡፡ በመድረኩ የክልሉና የከተማ አስተዳደሩ አመራር አባላትን ጨምሮ የፍትህ አካላት የስራ ሃላፊዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶችና የተለያዩ የህብረተሰብ ተወካዮች ተሳታፊ ሆነዋል።  
የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም