የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ኮሚሽነሮች - ኢዜአ አማርኛ
የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ኮሚሽነሮች
የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን የሕብረቱ የሥራ አስፈጻሚ እና አሥተዳደራዊ ክንፍ ነው።
ኮሚሽኑ የሕብረቱን የዕለት ተዕለት ሥራዎችን የሚያከናውን ሲሆን፤ ፖሊሲዎችን ይተገብራል።
በተጨማሪም የአፍሪካ ሕብረት አባል ሀገራት፣ ከቀጣናዊ ተቋማት እና አደረጃጀቶች ጋር ያላቸው ትብብር እንዲጠናከር የማስተባበር ሚና ይወጣል።
የሕብረቱን በጀት እና ሀብቶችም ያሥተዳድራል። የተለያዩ የአፍሪካ ሕብረት አደረጃጀቶች የተሰጣቸውን ኃላፊነት በሚገባ እንዲወጡም ድጋፍ ያደርጋል።
ኮሚሽኑ በሊቀ መንበር የሚመራ ሲሆን፤ ምክትል ሊቀ መንበር እና የተለያዩ ዘርፎች የሚመሩ ኮሚሽነሮችንም ይዟል።
በአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ ሊቀ መንበርነት የሚመራው የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን በሥሩ ሥድስት ኮሚሽኖች አሉት። እነሱም:-
- የግብርና፣ ገጠር ልማት ብሉ ኢኮኖሚና ዘላቂ ከባቢ አየር ኮሚሽን - በኢስዋቲኒው ሞሰስ ቪላካቲ የሚመራ፤
- የኢኮኖሚ ልማት፣ የንግድ፣ ኢንዱስትሪ እና ማዕድን ኮሚሽን - በኢኳቶሪያል ጊኒዋ ፍራንቺስካ ቻቹፕ ቤሎቤ የሚመራ፤
- የትምህርት፣ ሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ኮሚሽን - በብሩንዲያዊው ፕሮፌሰር ጋስፓርድ ባያንኪምቦና የሚመራ፤
- የመሠረተ ልማትና ኢነርጂ ኮሚሽን - በደቡብ አፍሪካዊቷ ሌራቶ ማታቦጅ የሚመራ፤
- የፖለቲካ ጉዳዮች፣ የሰላምና ደኅንነት ኮሚሽን - በናይጄሪያዊው አምባሳደር ባንኮሌ አዶዬ የሚመራ፤
- የጤና፣ ሰብዓዊ ጉዳዮችና የማኅበራዊ ልማት ኮሚሽን - በጋናዊቷ አምባሳደር አማ ትውም አሞን የሚመራ፤
ከአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ኮሚሽነሮች መካከል ሦስቱ ሴቶች ናቸው።
አንድ ኮሚሽነር ለአራት ዓመት የሚያገለግል ሲሆን፤ ኮሚሽነር ለመሆን በሚደረግ ምርጫ በድጋሚ ለመመረጥ መወዳዳር ይችላል።
የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር የሆኑት መሐሙድ አሊ ዩሱፍ እ.አ.አ በ2025 በአዲስ አበባ በተካሄደው 38ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባዔ ላይ በተካሄደ ምርጫ፤ ለአራት ዓመት በሊቀ መንበርነት እንዲመሩ መመረጣቸው ይታወሳል።
እንዲሁም አልጄሪያዊቷ አምባሳደር ሰልማ ማሊካ ሃዳዲ እ.አ.አ በ2025 በተካሄደው ምርጫ የኮሚሽኑ ምክትል ሊቀ መንበር ሆነው ተመርጠዋል።
አምባሳዳር ሰልማ ከሩዋንዳዊቷ ዶክተር ሞኒክ ንሳንዛባጋንዋ በኋላ፤ የአፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን ምክትል ሊቀ መንበር ሆነው የተመረጡ ሁለተኛ ሴት ባለሥልጣን ናቸው።
39ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባዔ የካቲት 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም፤ ከዚህ ቀደም ብሎ ደግሞ 48ኛው የአፍሪካ ሕብረት የሥራ አስፈጻሚ ምክር ቤት የካቲት 4 እና 5 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል፡፡
የዘንድሮው ጉባዔ “ዘላቂ የውኃ አቅርቦትና ደኅንነቱ የተጠበቀ የንጽህና አጠባበቅ ሥርዓቶችን ማረጋገጥ፤ ለአጀንዳ 2063 ግቦች ስኬታማነት” በመል መሪ ሐሳብ ይካሄዳል፡፡
ኢትዮጵያም ጉባዔው ስኬታማ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ዝግጅቷን አጠናቅቃለች።