አጀንዳ 2063 በአፍሪካውያን ኑሮ ላይ የሚጨበጥ ለውጥ እንዲያመጣ ማድረግ ይገባል- መሐሙድ አሊ ዩሱፍ - ኢዜአ አማርኛ
አጀንዳ 2063 በአፍሪካውያን ኑሮ ላይ የሚጨበጥ ለውጥ እንዲያመጣ ማድረግ ይገባል- መሐሙድ አሊ ዩሱፍ
አዲስ አበባ፤ ጥር 23/2018 (ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ሀገራት አጀንዳ 2063 ከአህጉራዊ ራዕይ ባለፈ የዜጎችን ኑሮ የሚቀይር ፕሮጀክት ለማድረግ በቁርጠኝነት እንዲሰሩ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ አሳሰቡ።
የአጀንዳ 2063 ትግበራ የሚከታተለው የሚኒስትሮች ኮሚቴ ዛሬ ስብሰባውን በበይነ መረብ አድርጓል።
የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀ መንበር መሐሙድ አሊ ዩሱፍ በዚሁ ወቅት እንዳሉት አዲሱ የህብረቱ አመራር አጀንዳ 2063 ውጤታማ ለማድረግ ከቃል የተሻገረ የፖለቲካ ቁርጠኝነትን በመላበስ አበክሮ መስራት ይገባዋል።
የአጀንዳ 2063 የ10 ዓመት የሁለተኛ ምዕራፍ የትግበራ እቅድ አህጉራዊውን ማዕቀፍ ለማፋጠን የሚያስችል ግልጽ ፍኖተ ካርታ እንዳለው አመልክተዋል።
ይሁንና አነስተኛ የፋይናንስ አቅርቦት፣ የትላልቅ ፕሮጀክቶች መጓተት እና የተቋማዊ አቅም ውስንነት የሚፈለገውን ውጤት አለማስገኘቱን ተናግረዋል።
ሊቀ መንበሩ ራዕይን ከፋይናንስ አቅርቦት፣ እቅድን የመፈጸም አቅምን ከመጨመር እና ክትትልን ከተጠያቂነት ጋር ማስተሳሰር ይገባል ነው ያሉት።
የአስተዳደር ሪፎርሞች ማጠናከር እና የፖሊሲ ማነቆዎችን ማስቀረት ቁልፍ እንደሆነም አንስተዋል።
የአፍሪካ ሀገራት ከአጀንዳ 2063ትን የአፍሪካውያን የዕለት ተዕለት ኑሮ ወደ መቀየር ምዕራፍ ለማሸጋገር በቁርጠኝነት ሊሰሩ እንደሚገባ ሊቀ መንበሩ ማሳሰባቸውን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።