መጣጥፍ - ኢዜአ አማርኛ
መጣጥፍ
ጥቂት ስለ አርቲፊሻል ኢንተሊጀንስ
Feb 18, 2025 29
አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ አዲሱ የዓለም የፉክክር መድረክ እየሆነ መጥቷል። በልብወለድ ወይም በምናብ የሚታሰቡ ፈጠራዎች፤ በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ እውን እየሆኑም ይገኛሉ። እ.ኤ.አ ከ2012 ወዲህ በከፍተኛ ደረጃ ዕድገት ያሳየው አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ በአሁኑ ጊዜ ከሰዎች የቀን ተቀን ሕይወት ጋር እየተዛመደ መጥቷል። በዕለት ተዕለት የሰዎች እንቅስቃሴ ውስጥ ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸውን የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መጠቀሚያዎች እንመልከት። 👉ቻት ጂፒቲ (ChatGPT): ጥያቄዎችን ለመመለስ፣ ሀሳቦችን ለማመንጨት እንዲሁም በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ መረጃዎችን ለማግኘት የሚረዳ ነው። 👉ግራመርሊይ (Grammarly) : በፅሁፍ ውስጥ የግራመር (ሰዋሰው) እንዲሁም የስርዓተ ነጥብ ስህተቶች የሚያርም የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መጠቀሚያ ነው። 👉ካንቫ (Canva) : የተለያዩ ግራፊክስ ስራዎችን በቀላሉ የሚሰራልን መጠቀሚያ ነው። 👉ኦተር ኤአይ (Otter.ai) : በድምፅ የምንናገራቸውን ወደ ፅሁፍ (text) የሚቀይር መጠቀሚያ ሲሆን በአብዛኛው በትምህርት ቤት ውስጥ ለሌክቸር ይጠቀሙታል:: 👉ክራዮን (Craiyon) : ፅሁፍ ብቻ በመፃፍ የምንፈልገውን ፎቶ ለመፍጠር የሚረዳ መጠቀሚያ ነው። 👉ሬፕሊካ (Replica) : የኤ አይ ቻት ቦት ሲሆን ስለ አዕምሮ ህክምና የሚያማክር እንዲሁም የግል የአዕምሮ ህክምና ምክር የሚሰጥ ነው። 👉ማይክሮሶፍት ቱ ዱ (Microsoft To Do): የቀን ሥራዎቻችንን ለማቀድ እና ለማደራጀት የሚያግዝ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መጠቀሚያ ነው። 👉ሄሚንግዌይ ኤዲተር (Hemingway Editor): የኦንላይን መፃፊያ ሲሆን አፃፃፋችን የጠራ እና ሀሳብን የያዘ እንዲሆን የሚያግዝ መጠቀሚያ ነው። 👉ጎግል አሲስታንት (Google Assistant): የቨርቹዋል አጋዥ መጠቀሚያ ሲሆን የቤት ውስጥ ስማርት መሳሪያዎችን ለመቆጣጠር፣ ጥያቄዎችን ለመመለስ እንዲሁም አስታዋሽ በመሆን ያገለግላል። 👉ጎግል ፎቶ (Google Photos): ፎቶዎችን ለማደራጀት እንዲሁም ለመፈለግ የሚረዳ የአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መጠቀሚያ ነው።
የአድዋን መንፈስ እንልበስ- ጠቅላይ ሚኒስትር ሚያ ሞትሌይ
Feb 18, 2025 66
ወርሃ የካቲት የጥቁሮች ወር ነው። ካሪቢያን ጥቁሮች በጥቁሮች የትግል ታሪክ ጉልህ አሻራ ያላቸው መሰረተ አፍሪካ ህዝቦች ናቸው። ካሪቢያን ዜጎች ኢትዮጵያን አብዝተው ይወዳሉ። ለመላው ጥቁር ሕዝቦች አንድነትና ትግል ንቀናቄ አድዋን እንደ እርሾና እሴት ያወሳሉ። በቅርብ በ38ኛው የአፍሪካ ሕብረት የመሪዎች ጉባዔ ላይ የታደሙት የባርቤዶስ ጠቅላይ ሚኒስትር ሚያ ሞትሌይ በሕብረቱ ጉባዔ ላይ ያደረጉት ንግግር በርካቶችን ያስደመመና ያስደነቀ ነበር። ከመልዕክታቸው ውስጥ ተከታዮቹን ሃሳቦች መዘናል፦ 👉 አድዋ በ24 ሰዓታት ውስጥ የአውሮፓዊያንን የራስ መተማመን ትምክህት ያሽመደመደ፤ የአፍሪካዊያንና ትውልድ አፍሪካዊያንን ልጆች መንፈስ ያጎመራ፣ መልካምነት ድል ያደረገበት፣ ብርሃን በጨለማ ላይ የነገሰበት ሁነት ነው። 👉 ዛሬ እናንተ ፊት የቆምኩት ይህን መንፈስ ታጥቄ ነው። አድዋ የፓን አፍሪካኒዝም እርሾ ነበር። 👉 የአድዋ ድል ለነጻነትና ትግል እንድንነሳሳ ባቻ ሳይሆን ፖለቲካዊ ነጻነት ድል እንድንቀዳጅ ምዕራፍ የከፈተ ድል ነው። አድዋ የአንድነት ውጤት ነው። 👉 እናንተ ፊት የቆምኩት የፓን አፍሪካዊነት ፈር ቀዳጆችን ሕልም ሰንቄ ነው። 👉 እኛ የካረቢያን ትውልዶች ከአፍሪካ ወንድምና እህቶቻችን ጋር ሕብረታችንን ማጠናከር እንሻለን። 👉 ትናንት በእኛ መከፋፈል ራሳቸውን ለበላይነት ያነገሱ ሃይሎችን እያሰብን አንድነታችንን አጠናክረን ነገን እንገንባ ወይም እንደ ትናንቱ ተነጣጥለን እንጥፋ የሚለው ምርጫ የኛ ፋንታ ነው። 👉 ስለዚህ የአድዋን መንፈስ ተላብሰን ከፊታችን የሚጠብቀንን መልከ ብዙ ፈተና በአንድነት እንጋፈጥ። 👉 ከአፍሪካ ውጭ የጥቁሮች ምድር ከሆነችው ባርባዶስ ተነስቼ ኢትዮጵያ የተገኘሁት ለአፍሪካና ካረቢያን ህዝቦች አንድነትና ወንድማማችነት ጥሪ ነው። 👉 ግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃይለሥለሴ በዓለም ላይ አንደኛና ሁለተኛ መደብ ዜጋ መኖር የለበትም እንዳሉት ዛሬም በየትውልዱ በዓለም ላይ ኢ-ፍትሃዊነትና አግላይነት ስርዓት ይወገድ ዘንድ መታገል አለብን። ለዚህ ደግሞ የአድዋ ድልና የፓን አፍካዊነት መንፈስን እንልበስ። 👉 የጋራ መዳረሻችንን ለመቀየስ ከወሬ ይልቅ ተግባር ላይ አተኩረን በትጋት እንስራ። የትናንት ቁስልን እያከክን ሳይሆን ብሩህ ነገን ለመገንባት በጋራ እንቁም። 👉 ከፊታችን የተደቀነ አደገኛ ፈተና እንዳለ ተገንዝበን ፈተናውን በአንድነት ለመጋፈጥ ሞራላዊ ግዴታችንን እንወጣ። 👉 የአድዋን መንፈስ እንልበስ!
አዲስ አበባ በአሕመድ ሴኩ ቱሬ አንደበት
Feb 15, 2025 65
(62 ዓመታት ወደኋላ) ________________ አሕመድ ሴኩ ቱሬ ከቀደምት የፓን አፍሪካዊነት አቀንቃኞች አንዱ ነበር። በፈረንሳይ ቅኝ ግዛት ስር በነበረቸው የምዕራብ አፍሪካዊነቷ ሀገረ-ጊኒ የነጻነት ታጋይና ፖለቲከኛ ናቸው። ድሕረ ነጻነት የሀገሪቷ የመጀመሪያው ፕሬዚዳንት ሆነዋል። በፈረንጆቹ አቀጣጥርግንቦት 1963 የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ምስረታ ላይ ከታደሙና አስደማሚ ንግግር ካሰሙ መሪዎች መካከል አንዱ ሴኩ ቱሬ ነበሩ። ለዛሬ ከፕሬዝዳንት አሕመድ ሴኩ ቱሬ አዲስ አበባን እና ኢትዮጵያን በወቅቱ የገለጹበትን መንገድ እነሆ ብለናል። “…. አዲስ አበባ የታሪክ ክስተት መውጠኛ ስፍራ ናት። በአፍሪካ አወንታዊ የለውጥ ሽግግር ታሪክ መቁጠሪያ ነጥብ ሆናለች። ይህ ቅጽበት የአፍሪካ የተሟላ አርነት ማብሰሪያ ነው፤ የአፍሪካ ሰው ከነምጣኔ ሀብታዊ፣ ማህበራዊ፣ ወታደራዊ፣ ባህላዊና መንፈሳዊ ውቅሩ ነጻ የሚወጣበት። ይህ ስፍራ አፍሪካዊያን መንግስታትን ውጤታማ የሚያደርግ የፈጠራ ክዋኔዎች የመለኮሻ ዘመንም ነው። ለምን ቢሉ አፍሪካዊያን ወደ አንድ በመመጣት ህዝባቸውን ከሰቆቃ እንዲያገግም፣ የጋራ ስልጣኔ እንዲያንሰራራ፣ ሰብዓዊ እሴቶችና ባህላቸው ፈጣን እመርታ እንዲያመጣ ግብ የሰነቁበት ነውና። የኢትዮጵያ ሕዝብ ትልቅ ነው። ኢትዮጵያዊያን ለአፍሪካ ነጻ መውጣት በጀግንነት ተዋግተዋል። የሕዝብ ነጻነት እንዲጠበቅ ብሎም ሰዎች ያለማንም የውጭ አካል ጣልቃገብነት መብታቸው ተከብሮ መዳረሻቸውን በራሳቸው ይተልሙ ዘንድ መንገድ የጠረጉ እና የራሳቸውን ጉዳይ በተሟላ ሉዓላዊነት እንዲፈጽሙ በተግባር ያሳዩ ህዝቦች ናቸው። ዛሬ በኢትዮጵያ ርዕሰ መዲና አዲስ አበባ የአፍሪካ ጉባዔ እየተካሄደ ነው። ይህም ኢትዮጵያ ምንጊዜም በአፍሪካ ታሪክ ገጾች ውስጥ ደማቅ አሻራ አንብራለች። መላው የአህጉሪቷ ህዝብ የመለወጥ መሻቱን በቅጡ እንዲገነዘብ የተካሄደ ሁነት ነው። በ1885ቱ(በአውሮፓዊያን አቆጣጠር) የበርሊን ጉባዔ በኢኮኖሚ የጠገቡ ስርዓት አልበኛ የአውሮፓ መንግስታት ስልጣኔያቸውን ለማስፋፋት ሲሉ ያላቸውን ሀይል ተመክተው አፍሪካን እንደ ኬክ ቆራርሰው ሊቀራመቱ ተሰባስበው ነበር። ዛሬ ግንቦት 1963(በአውሮፓዊያን) ግን ምርጥና ሐቀኛ የአፍሪካ ልጆች ስለራሳቸው እና ስለእናት ምድር አፍሪካ ታምነው በንጹህ ማንነት የጋራ መዳረሻ መንገድ ለመቀየስ አዲስ አበባ ተሰባስበው እየመከሩ ነው። የአፍሪካ ትንሳኤዋ ዛሬ ነው። አፍሪካ በአንድ ነጠላ መንግስት ህጋዊ መልክ ትይዝ ዘንድ ልዩ መተዳደሪያ ሰነድ(ቻርተር) ማለትም አፍሪካዊያንን በወንድማማችነት፣ በማይናወጥ አጋርነት፣ በሰዎች መብትና ጥቅም፣ በሰላምና ነጻነት እንዲሁም በፍትህ መርሆች ውህደት የሚፈጥሩበት አጋጣሚ ነው። የአዲስ አበባ ጉባዔ የዛሬን አፍሪካ ችግሮች ምላሽ በመስጠት ላይ ብቻ የተወሰነም አይሆንም። አፍሪካ የዓለም አካል መሆኗን ልብ ይሏል። በዓለም ላይ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ የሰው ልጅ ሕይወት፣ ሰላም፣ ደህንንትና ዕድገት መንስኤ የሆኑ የጋራ ተግዳሮቶች ሁሉ አፍሪካን ይገዷታል…”።
የአፍሪካውያን የዛሬ ስራ ለነገ ተስፋቸው
Feb 14, 2025 103
በዓለም በትልቅነቷ በሁለተኝነት የምትጠቀሰው አፍሪካ የህዝብ ቁጥሯ በ2024 (እ.ኤ.አ) አንድ ነጥብ አምስት ቢሊዮን መድረሱን መረጃዎች ያመለክታሉ። አህጉሪቷ በተፈጥሮ ሃብት የታደለች፣ የሰጡትን የሚያበቅል ለም አፈር ያላት፣ ከራሷ አልፋ ለሌሎች የምትተርፍ መሆኗም በብዙዎች የተመሰከረለት ነው። ይሁንና አህጉሪቷ ለበርካታ ዓመታት በጦርነት፣ በበሽታ፣ በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ አደጋዎች ስትጠቃ ኖራለች። ከተመሰረተ 50 ዓመታትን የተሻገረው የቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት የወቅቱ የአፍሪካ ህብረት አባል አገራት "እ.ኤ.አ በ2063 መሆን የምንፈልገው" ብለው የተለያዩ እቅዶችን ነድፈው ወደ ተግባር ገብተዋል። ''እኛ አፍሪካውያን በ2063 መሆን የምንፈልገው'' በሚል ባሰፈሩት አጀንዳ በርካታ የአህጉሪቷ የልማትና የብልጽግና ትልሞች ተቀምጠዋል። በዚህም ሁሉን አቀፍ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ልማት የተረጋገጠባት፣ በልማትና በኢኮኖሚ የተዋሃደች፣ ሰላምና ደህንነቷ የተጠበቀና በዓለም አቀፍ መድረክ ተሰሚነቷ የጎለበተ አህጉር መፍጠር ይገኙበታል። በኢኮኖሚ የፈረጠመች፣ የምግብ ሉዓላዊነቷን ያረጋገጠችና ለዜጎቿ ምቹና አስተማማኝ አህጉር የማድረግ እቅዱን ለማሳካት የተለያዩ ጥረቶች ተጀምረዋል። የአገራቷ መሪዎችም እነዚህን የልማት እቅዶች ከየአገራቸው ነባራዊ ሁኔታ ጋር በማጣጣም ለገቢራዊነቱ ጥረት ሲያደርጉ ይስተዋላል። አፍሪካ በ50 ዓመታት ለማሳካት የያዘችው አጀንዳ ሁሉን አቀፍ የልማት እቅድ፣ ከዓለም ተለዋዋጭ ነባራዊ ሁኔታና በአፈጻጸም ቁርጠኝነት ክፍተት እስካሁን የሚፈለገውን ያህል ውጤት ያለመመዝገቡም ይገለጻል። መሪዎቹ ይህን እቅዳቸውን ወደ ተግባር ለመቀየር የነበራቸው ቁርጠኝነት ማነስ፣ የውጭ ተጽእኖ ማየል ዕቅዶቹ እንዳይሳኩ ምክንያት ሆነዋል። በአየር ንብረት ለውጥ ከፍተኛ ተጽዕኖን የምታስተናግደው አፍሪካ አሁንም ቢሆን ተደጋጋሚ ድርቅና ጎርፍን እንዲሁም ተላላፊና ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች ዜጎቿን እየፈተኑ ይገኛሉ። የምርትና ምርታማነት እጥረት፣ የሰለጠነ የሰው ሃይልና ቴክኖሎጂ አቅም ውስንነት፣ የሌሎች አገራት ጣልቃ ገብነትና ሌሎች ችግሮችን በመፍታት አጀንዳዋን ለማሳካት ብዙ ይቀራታል። አፍሪካ በ50 ዓመታት ውስጥ ለመሳካት ያቀደችውን በተግባር ለማጠናቀቅ 38 ዓመታት ይቀሯታል። በዚህ ረገድ የተወሰኑ አገራት የተሻለ ኢኮኖሚ በማስመዝገብ፣ የአየር ንብረት ለውጥን በመከላከል፣ የምግብ ዋስትናን በማረጋገጥና፣ መሰረተ ልማትና ቴክኖሎጂን በማሟላት የተሻለ ዕድገት ማስመዝገባቸው ይነገራል። በአህጉሪቷ በተመሰረቱ የተለያዩ ጥምረቶች አገራት እርስ በእርስ በመሰረተ ልማትና በሃይል በማስተሳሰር ረገድ መልካም የሚባሉ ጅምሮች ታይተዋል። ይሁንና የዓለምን ተለዋዋጭ የፖለቲካ፣ ኢኮኖሚና ማህበራዊ ጉዳዮች በአግባቡ በመረዳት የዜጎችን ህይወት በተጨባጭ መቀየር፣ ሰላማዊ፣ በኢኮኖሚ የዳበረች፣ በዓለም መድረክ እኩል ድምጽ ያላት አህጉር የመፍጠር እቅዱን እውን ለማድረግ በርካታ ቀሪ ስራዎች መኖራቸው የአደባባይ ሀቅ ነው። እያንዳንዱ አፍሪካዊ ዜጋ አጀንዳ 2063ን በአግባቡ ተገንዝቦ ለትግበራው የድርሻውን መወጣት እንዲችልም በቂ የግንዛቤ ስራ ሊሰራ ይገባል። የአፍሪካ መሪዎች በአጀንዳ 2063 የተያዙ ግቦች በትክክል እንዲተገበሩ ዜጎቻቸውን አስተባብረው በቁርጠኝነት መስራት ግድ ይላቸዋል። የአጀንዳ 2063 እውን መሆን ዋነኛ ተጠቃሚ የሚያደርገው የአህጉሪቷን ዜጎች እንደመሆኑ እቅዱን ለማሳካት አሻራቸውን እንዲያሳርፉ ያላሰለሰ ጥረት ማድረግ ለነገ የማይባል ተግባር ነው። የአፍሪካ አገራት የጋራ ጉዳዮቻቸው ላይ ለመምከርና የአህጉሪቷን መጻዒ ዕድል የተሻለ ለማድረግ በአንድ ጥላ በሚያሰባስባቸውና በዓመት ሁለት ጊዜ በሚካሄደው የአፍሪካ ህብረት ጉባዔ ላይ ይገናኛሉ።
ኢትዮጵያ እና የሕብረቱ ወሳኝ አካል የሆነው ምክር ቤት
Jan 17, 2025 535
የአፍሪካ ሕብረት ቁልፍ ተቋም ነው- የሕብረቱ የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት። የፊታችን የካቲት ወር መጀመሪያ ሳምንት ላይ በሚደረገው የሕብረቱ የመሪዎች ጉባዔ ከሚቀረቡ ዝርዝር አጀንዳዎች አንዱ የዚህ ምክር ቤት አባላት ምርጫ እንደሚሆን ይጠበቃል። ኢትዮጵም በቅርቡ ለምክር ቤቱ አባል ለመሆን ፍላጎቷን ይፋ አድርጋለች። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ የምክር ቤቱ አባል ለመሆን ያላትን መሻት በአዲስ አበባ ለሚገኙ የአፍሪካ ሀገራት አምባሳደሮች አብስረዋል። ለመሆኑ የሕብረቱ የሰላምና የደህንነት ምክር ቤት ስራው ተልዕኮና ሚና ምንድነው? አባላቱም እንደ ሀገር ምን ፋይዳ ይሰጣቸው ይሆን የሚለውን እንናስቃኝዎ! የምክር ቤቱ ለመመስረቻ ጥንስስ የተጠነሰሰውና የማቋቋሚያ ሕግ ማዕቀፍ የጸደቀው በአውሮፓዊያኑ 2002 በደርባን(ደቡብ አፍሪካ)በተካሄደው የአፍሪካ ሕብረት መደበኛ ስብስባ ነበር። በአውሮፓዊያኑ ታኅሣሥ 2003 ወደ ስራ ገባ። ባለፈው ዓመት (ግንቦት 2016 ዓ.ም) ምክር ቤቱ 20ኛ ዓመት የምስረታ ቀኑን በአዲስ አበባ አክብሯል። ምክር ቤቱ በአህጉሪቷ ግጭቶች እንዳይከሰቱ አስቀድሞ መከላከል፣ የግጭት አስተዳደርና አፈታት ላይ ከፍተኛ የውሳኔ ሰጪ አካል ነው። በአህጉሪቷ ለሚከሰቱ ግጭቶች ጊዜውን የጠበቀ እና በቂ ምላሽና ቅድመ ማስጠንቀቂያ ይሰጣል። ለአፍሪካ የሰላም እና ደህንነት ማዕቀፍ (African Peace and Security Architecture) ቁልፍ ምሰሶ ነው። የምክር ቤቱ አወቃቀር፣ ተልዕኮና ሚና ከአወቃቅር አኳያ ምክር ቤቱ ዕኩል ድምጽ ያላቸው 15 አባል አገራት ይኖሩታል። አባላቱም በሕብረቱ የስራ አስፈፃሚ ምክር ቤት ይመረጣሉ። በመሪዎች ጉባዔ አባልነታቸው ይጸድቃል። ከአባላቱ መካከል አምስቱ ለሶስት ዓመታተ፤ ቀሪዎቹ ለሁለት ዓመታት የሚቆይ ስልጣን አላቸው። ምክር ቋሚ አባል አገር የለም። የአባልነት ጊዜ የጨረሱ ሀገራት ግን ድጋሚ የመመረጥ መብት አላቸው። አባላት የሚመረጡት ግን በቀጣናዊ ውክልና እና በተራ ቅደም ተከተል መርህ ነው። ይኼውም ማዕከላዊ፣ ምሥራቃዊ፣ ደቡባዊ እና ሰሜናዊ ቀጣናዎች ሶስት አባል ሀገራት ሲሆኑ የምዕራብ ቀጣና ግን አራት አባል አገራት ይኖራቸዋል። በምክር ቤት ሕገ ደንብ መሰረት ለምክር ቤቱ አባል ለመሆን ቅድመ ሁኔታዎች አሉ። ይሄውም የአፍሪካ ሰላምና ደህንነትን በማስተዋወቅና በማረጋገጥ ያለው አስተዋጽኦ፣ በቀጣናዊና በአህጉር አቀፍ ደረጃ በሰላም ማስከበር እና በሰላም መፍጠር ውስጥ ያለው ሚና፣ ቀጣናዊና አህጉር አቀፍ የግጭት መፍቻ ኢኒሺቲቮች ለመሳተፍ ያለው ፍላጎት እና ኃላፊነት ለመውሰድ ያለው ቁርጠኝነት፣ ለአፍሪካ ህብረት የሰላም ፈንድ የሚያደርገው አስተዋጽኦ፣ ለሕገ መንግስት አስተዳደር፣ የሕግ የበላይነት እና የሰብዓዊ መብቶች ያለው ከበሬታ እንዲሁም ለአፍሪካ ሕብረት የፋይናንስ መዋጮ ግዴታዎች ያለው ተገዢነት እና ቁርጠኝነት አንድን አገር አባል ሆኖ እንዲመረጥ የሚያስችሉት መስፈርቶች ናቸው። ምክር ቤት ከሕብረቱ ኮሚሽን ሊቀመንበር ጋር በመጣመር ከስር የተመላከቱ ስልጣንና ተግባራቱ ተሰጥቶታል። . ዘር ማጥፋትና በሰብዓዊነት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች ሊያመራ የሚችል የግጭት አዝማሚያን መተንበይ፣ አስቀድሞ በመከላከልና የግጭት መንስዔዎችን ለይቶ ፖሊሲ መቀየስ። የጦር ወንጀሎች፣ ዘር ማጥፋት እና የሰብዓዊነት ወንጀሎች ሲፈጸሙ ለመሪዎች ጉባዔ ሕብረቱን ወክሎ ጣልቃ መግባት የሚችልበትን ምክረ ሀሳብ ያቀርባል። . ለግጭቶች በሰላም እንዲፈቱ በማስቻል ሰላም መገንባት ላይ ይሰራል።የአፍሪካ ሕብረት አጠቃላይ የጋራ የመከላከያ ፖሊሲ ይተገብራል። . ለሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች ፈቃድና ስምሪት ይሰጣል፤ የሰላም አስከባሪ ኃይል የስራ ኃላፊነት ጨምሮ ተልዕኮውን የተመለከቱ መመሪያዎችን ያወጣል። . በአፍሪካ ሕብረት አባል አገራት ኢ-ሕገመንግስታዊ የመንግስት ለውጥ ሲኖር ማዕቀብ ይጥላል። . የፀረ-ሽብርተኝነትን ዓላም አቀፍ ስምምነቶች የአባል ሀገራት ትግበራን ይከታተላል። በመልካም አስተዳደር፣ በሕግ የበላይነት፣ የሰብዓዊ መብቶች እና መሰረታዊ ነጻነቶች እና ሰብዓዊ መብቶች ላይ ጥበቃ ያደርጋል። ቀጣናዊና አህጉራዊ የተቀናጀ የሰላምና ደህንነት አሰራርን መፈጸሙንም እንዲሁ። በጦር መሳሪያ ቁጥጥርና ትጥቅ የማስፈታት የሕግ ማዕቀፎችን ትግበራ ይደግፋል። . የአፍሪካ ሕብረት አባል አገራትን ነጻነት እና ሉዓላዊነትን ስጋት ላይ የሚጥሉ የኃይል እርምጃዎችን በመመርመር እርምጃ ይወስዳል። . በሰው ሰራሽ እና የተፈጥሮ አደጋዎች ወቅት ለሰብዓዊ ድጋፍ ያስተባብራል። አፍሪካ ሕብረት ኮሚሽን የሰላምና ደህንነት የስራ ክፍል ውስጥ የሚገኘው የምክር ቤቱ ሴክሬተሪያት ለምክር ቤቱ የኦፕሬሽን ስራዎች የቀጥታ ድጋፍ ያደርጋል። ምክር ቤቱ በአህጉሪቷ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ስርዓት፣ “Panel of the Wise” በተሰኘው የአፍሪካ ሕብረት የማማከር አደረጃጀት፣ በአፍሪካ ተጠባባቂ ኃይል እና የሕብረቱ የሰላም ፈንድ ድጋፍ ይደረግለታል። በምክር ቤቱ በስሩ ያሉት ወታደራዊ አባላት እና የባለሙያዎች ቡድን ኮሚቴዎች፣ የአፍሪካ የሰላምና ደህንነት ማዕቀፍ (APSA)፣ የአፍሪካ የሴቶች ግጭት መከላከል እና የሰላም ድርድር ኔትወርክ (FemWise–Africa) እንዲሁም የሰላምና ደህንነት ማስከበር ተልኮዎች ሌሎች ደጋፊ አካላት ናቸው። ምክር ቤቱ ከቀጣናዊ የኢኮኖሚ ተቋማት እና ከሌሎች ቀጣናዊ አደረጃጀቶች ጋር ግጭትን አስቀድሞ መከላከል፣ አስተዳደር እና መፍትሄ ላይ በጋራ ይሰራል። ከተባበሩት መንግስታት የጸጥታው ምክር ቤት እና ሌሎች መሰል ዓለም አቀፍ ተቋማት፣ የሲቪክ ማህበረሰብ ተቋማት እንዲሁም ፓን-አፍሪካ ፓርላማ እና የአፍሪካ የሰብዓዊና የህዝብ መብቶች ኮሚሽንን ጨምሮ ከሌሎች የአፍሪካ ህብረት አደረጃጀቶች ጋር በሰላምና ደህንነት ጉዳዮች ላይም በትብብር እየሰራ ይገኛል። የአፍሪካ የሰላም እና ደህንነት ምክር ቤት ኃላፊነቶች፣ አደረጃጀቶች እና የቅንጅት አሰራር ማዕቀፎች በአህጉሪቷ የሰላም እና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ ያለውን ቁልፍ የውሳኔ ሰጪነት አቅም የሚያሳይ ነው። ኢትዮጵያ እና ምክር ቤቱ ኢትዮጵያ ለመወዳደር የፈለገቸው ለሶስት ዓመት (በአውሮፓዊያኑከ2025 እስከ 2027) ድረስ ነው። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) የሕብረቱ አባል ሀገራት አምባሳደሮች ለአፍሪካ የዋለችውን ታሪካዊ ሚና ከግንዛቤ በማስገባት በውሳኔ ሂደቱ ድጋፋቸውን እንዲሰጡ ጠይቀዋል። በርግጥ በአፍሪካ ሰላምና ደህንነት ያላት ቁልፍ ሚና ተገቢነቱ አያጠራጥርም። ኢትዮጵያ በአፍሪካ ሰላምና መረጋጋት ለረጅም ዘመናት በቁርጠኝነት ሰርታለች። የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት የአፍሪካ ጉዳዮች ከፍተኛ ተመራማሪ ሄኖክ ጌታቸው (ዶ/ር) ኢትዮጵያ በተለያዩ ጊዜያት የአፍሪካ ሕብረት የሰላምና ደህንነት ምክር ቤት አባል ሆና ማገልገሏን ያስታውሳሉ። ምክር ቤቱ የአሁኑን ስያሜውን ከማግኘቱ በፊት በቀድሞ የአፍሪካ አንድነት ድርጅት (OAU) ማዕቀፍ ከእ.አ.አ 1993 እስከ 2000 ባለው ጊዜ አባል ሆና ማገልገሏን ገልጸዋል። በአፍሪካ ሕብረት ደግሞ በአውሮፓዊያኑ ከ2004 እስከ 2010 እንዲሁም ከ2014 እስከ 2016 አገልግላለች። ኢትዮጵያ የምክር ቤቱ አባል ሆና ብትመረጥ ብሔራዊና ቀጣናዊ ፍላጎቶቿንና ጥቅሞቿን ከማስጠበቅ እና አንጻር ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታ እንደምታገኝ ሄኖክ(ዶ/ር) ይናገራሉ። የምክር ቤቱ አጀንዳዎች ከብሔራዊ ጥቅሞቿ ጋር አጣጥሞ ለመሄድና ፍላጎቶቿን የሚጻረሩ ጉዳዮች ለመከላከል ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥርላትም በማንሳት። የአፍሪካ ዋንኛ የሰላምና ጸጥታ ጉዳይ አብዛኛውን ትኩረቱን አፍሪካ ቀንድ ከማድረጉ አንጻር ኢትዮጵያ በአካባቢው ባሉ ጉዳዮች ላይ ያላት ሚና እንዲጎለብት አስተዋጽኦ ያደርጋል ነው ያሉት ከፍተኛ ተመራማሪው። ቀጣናው ስትራቴጂካዊ ጠቀሜታና ዓለም አቀፍ ትኩረትን የሚስብ መሆኑ ያሉ ችግሮች መፍትሄ እንዲያገኙ የበኩሏን ድርሻ መወጣት እንደምትችልም ጠቅሰዋል። ኢትዮጵያ አባልነት የሕብረቱ የመመስረቻ ቻርተርና የህግ ማዕቀፎች እንዲጠበቁ፣ አህጉራዊ አጀንዳዎችን ለማራመድ፣ ሰላምና ጸጥታን ለማስፈንና በቀጣናው ከምትጫወተው ሚና አንጻር በርካታ ጠቃሜታዎችን እንደምታገኝ ተናግረዋል። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ የምክር ቤቱ አባል ለመሆን የተሻለ የተወዳዳሪነት ብልጫ እንዳላት ያነሳሉ። ለምን ቢባል አንድም ኢትዮጵያ በሩዋንዳ፣ በሱዳን፣ በደቡብ ሱዳን፣ በላይበሪያ፣ በኮንጎ፣ በሶማሊያ እና በሌሎች የአፍሪካ አገራት በሰላም ማስከበር ተሳትፎ በማድረግ ያላት ልምድ ነው። አንድም የአፍሪካ ሕብረት ዋና መቀመጫ መሆኗና ከዚህ ቀደም በምክር ቤቱ የነበራት ግልጋሎት እንደ የተወዳዳሪነት ብልጫ እንድታገኝ ያስችላታል። አባልነቷን ለማረጋገጥ ግን ከሀገራት ጋር የሁለትዮሽ ውይይቶችና ሌሎች የተቀናጀ የዲፕሎማሲ ስራ ማከናወን ይጠበቃል ይላሉ። ምከር ቤቱ በሕብረቱ የሰላም እና የደህንነት ምክር ቤት የአፍሪካ የሰላምና ደህንት ጉዳዮች ከፍተኛ የውሳኔ ሰጪ አካል በመሆኑ አባል ብትሆን ካላት ታሪካዊ አበርክቶ አኳያ ይበልጥ ለአህጉራዊ ሰላምና ደህንነት ገንቢ ሚና እንደምትጫወት ዕሙን ነው።
ወንዞቿን ከብክለት ወደ ትሩፋት ለመለወጥ የተነሳችው አዲስ አበባ
Jan 13, 2025 404
አዲስ አበባ ከተቆረቆራች አንድ ከግማሽ ምዕተ ዓመት ልትደፍን ጥቂት ዓመታት ይቀራታል። ከተማዋ በዘመናዊት ኢትዮጵያ ታሪክ ዑደት አስኳል ሆና ሁሉን አስተናግዳለች። ዕድል ቀንቷት ከኢትዮጵያዊያን አልፋ የአፍሪካዊያን መዲና ሆናለች። ዘመን ችሯት የዓለም ዲፕሎማሲ ማዕከል አድርጓታል። ከአፍሪካ ወደ ዓለም፤ ከዓለም ወደ አፍሪካ መግቢያና መውጫ በር ናት። የሀገሪቷ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ዕድገት የስበት ማዕከል ናት። በፍጥነት ያደገችና ነዋሪቿን ያበዛች፤ ምጣኔ ሀብትን ያጎለመሰች ከተማ ናት። ዳሩ የከተሜነት መዋቅራዊ ፕላኗ አኳያ ውስንነቶች እንደሚስተዋልባት በባለሙያዎች ዘንድ ይነሳል። ትውልድን ታሳቢ ያደረገ ዘመን ተሻጋሪ፣ ለኑሮ ምቹና ስሟን የሚመጥን የክትመት ዕቅድ ይዛ ባለመጓዟ ውበትም፤ ኑረትም፣ ምቾትም አጉድላለች። በጽዳትና ውበቷ ረገድ በእንግዶቿም ዘንድም ለትቸት ተጋልጣ ታውቃለች። ከአዲስ አበባ ድክመቶች አንዱ የብዙ ወንዞች ባለቤት ሆኗ አንዱንም እሴት ጨምራ ወደ ሀብትትነት አለመቀየሯ ነው። ፈሳሽ ወንዟን አልምታ በውበት አለመፍሰሷ። በመዲናዋ ከ76 ያላነሱ ዋና እና ገባር ወንዞች ይገኛሉ። ዳሩ በየዘመኑ የከተማ ልማት ዕቅዶች የወንዝ ዳርቻን ታሳቢ ባለማድረጋቸው ወንዞቿ ለገጽታዋ ውበት ሳይሆን ሳንካ ሆነዋታል። የከተሜነት ወጓ ከወንዞቿ ልማት ጋር አልተመራም። የሰዎች አሰፋፈር ከዓለም አቀፋዊ የከተሜነት ልክን አልጠበቀም። ይህ ደግሞ ወንዞች ለነዋሪዎቿ ጠንቅ እንጂ ትሩፋት እንዳይሆኑ አድርጓል። በርካታ ሀገራት ከተሞች ጥቂት ወንዞቻቸውን ለጌጥም፤ ለበረከትም አውለዋል። ባለበዙ ወንዞች ባለቤቷ አዲስ አበባ ግን "ጽድቁ ከርቶ..." እንዲሉ ከወንዞቿ ጥቅሟ ቀርቶ፤ ጠንቋ በዝቶ ቆይታለች። ወንዞቹን ለምተው ለዘርፈ ብዙ አገልግሎት ከመዋል ይልቅ ለብክለት ተጋልጠው ለሕዝብ ጤና ጠንቅ ነበሩ። በክረምት ወራትም ጎርፍ እየተሞሉ ነዋሪዎችን ለአደጋ አጋልጠዋል። እነሆ አሁን የዘመናት ክፍተቷን ለመቅረፍ ተነስታለች። ከተማ አቀፍ የወንዝ ዳርቻ ልማቶች ተጀምረዋል። የመዲናዋን ወንዞች ከሕዝብ ጤና ጠንቅነት ወደ ጥቅም የመለወጥ ተግባር እየተከናወነ ይገኛል። በአዲስ አበባ ከሚፈሱ ወንዞች መካከል እስካሁን አንድ ወንዝ ለቱሪስት መስህብነት፣ ለመዝናኛነትና ለሌላ አገልግሎት ለማዋል የተሰራ የተፋሰስ ልማት እየተከናወነ ነው። የከተማዋ ከንቲባ አዳነች አቤቤ የበርካታ ሀገራት ከተሞች የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ወንዞችን አልምተው ለቱሪስት መነሃሪያ እንዲሆኑ በማስቻል ለቱሪዝም ዘርፍ እመርታ ወሳኝ ድርሻ እንዲይዙ ማድረጋቸውን ይጠቅሳሉ። አዲስ አበባ ግን በርካታ ወንዞችን ታቅፋ ይህን መልካም ዕድል አልምታ ሳትጠቅም በመቆየቷ ቁጭት የሚፈጥር ጉዳይ እንደሆነ ያነሳሉ። እናም እየተከናወነ ያለው የወንዝ ዳርቻ ልማት የህብረተሰቡን አኗኗር ብቻ ሳይሆን ለተፋሰስ ልማትም ወሳኝ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። የአዲስ አበባ ወንዞች ከጠንቅነት ወደ ህዝብ ጥቅምነት የመለወጥ ስራዎች እንደቀጠሉ ከንቲባዋ አብስረዋል። በዚህም አዲስ አበባ ካሏት 76 ወንዞች መካከል አንድ ሶስተኛው ትልልቅ ወንዞቿ ለቱሪስት መዝናኛ አገልግሎት መዋል የሚችሉ ናቸው ብለዋል። ከነዚህም መካከል እስካሁን ሁለት ወንዞችን በወንዝ ዳርቻ ልማት በማስገባት ወደ ዘርፈ ብዙ ጥቅም የመለወጥ ጉዞ መጀመሩን ተናግረዋል። በትናንትናው ዕለት የከተማዋ አመራሮች እየተከናወኑ ያሉ የኮሪደር ልማቶችን ጎብኝተው ነበር። ከተጎበኙ የከተማ ልማት ስራዎች መካከል የቀበና ቁጥር-1 እና 2 እንዲሁም ከእንጦጦ-ፍሬንድ ሽፕ- ፒኮክ የወንዝ ዳርቻ ልማት ይገኝበታል። ከንቲባዋ በዚሁ ወቅት እንዳሉት የወንዝ ዳርቻ ልማት ከብክለት ነጻ አካባቢን በመፍጠር፣ ከተማዋን ጽዱና አረንጓዴ በማድረግና በሽታን በመከላከል ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል። የእንጦጦ-ፍሬንድ ሽፕ- ፒኮክ የወንዝ ዳርቻ ልማት የተለያዩ ፓርኮችን በማስተሳሰር በፕላን የተገነባ ከተማን እውን ማድረግ የሚያስችል እንደሆነ በማብራራት። በቀበና ቁጥር 2 እንዲሁም ከእንጦጦ- ፍሬንድ ሽፕ- ፒኮክ የወንዝ ዳርቻ አፍንጮ በር አካባቢ የመጓተት ችግሮችን በመቅረፍ ስራው በፍጥነት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸዋል። 70 ደረጃ እና 40 ደረጃ ታሪካዊ ቅርስነታቸውን ጠብቀው እየታደሱ እንደሚገኙ ገልጸው፤ ከዕይታ ተደብቆ የቆየውን የራስ መኮንን ሀውልት ከቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን ጋር በመተባበር ዕድሳት ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ፒያሳ አካባቢ እየተሰራ የሚገኘው የወንዝ ዳርቻ ልማት አለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ የሩጫ፣ የሳይክል፣ የመዋኛና ሌሎች ቦታዎችን ነው። ልማቶቹ አለም አቀፍ ስፖርታዊ ውድድሮችንና ሁነቶችን ለማስተናገድ የሚያስችሉ እንደሆኑ ከንቲባዋ በጉብኝቱ ወቅት አብራርተዋል። የህዝብ መሰብሰቢያ አዳራሾች፣ ፓርኪንግ፣ የታክሲ ተርሚናል፣ ሱቆችንና ሌሎች ልማቶችን አካቶ እየተሰራም ነው። ፕላኑን የጠበቀ ዘመናዊ ከተማን እውን የሚያደርግ ከንቲባዋ ጠቁመዋል። የወንዝ ዳርቻን ጨምሮ የአዲስ አበባ ከተማ አቀፍ የልማት ስራዎች ዘመናዊ ከተማን ያሟሉ በመሆኑ ለአዲስ አበባ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነትን ይጨምራሉ።
የምግብ ሉዓላዊነት፤ ከተረጂነት እና ጠባቂነት መላቀቂያ መንገድ
Jan 10, 2025 321
ኢትዮጵያ ራሷን ከተረጂነት ለማላቀቅ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ በትኩረት እየሰራች ትገኛለች። የዜጎችን የምግብ ፍላጎት በራስ የምርት አቅም የመሙላት ስራ በማከወን ከውጭ አገራት ምርት ጠባቂነት ለመላቀቅ እየተከናወኑ ያሉ ስራዎች ውጤት እያስገኙ ነው። ኢትዮጵያ በስንዴ ልማት ከልመና ወጥታ ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ውጭ ገበያ መላክ መጀመሯ ትልቅ ታሪካዊ ድል ነው። ከውጭ የኢኮኖሚ ጥገኝነት በመላቀቅ የዜጎችን የምግብ ሉዓላዊነት ለማስከበር በስንዴ ልማት የተመዘገበውን ስኬት በሌሎች የግብርና መስኮች ለመድገም በመሰራት ላይ ይገኛል። በሩዝ፣ አትክልትና ፍራፍሬን ጨምሮ ሻይ ቅጠልና ሌሎች የተለያዩ ሰብሎች ላይ እየተከናወነ ያለው ስራ ተጨባጭ ውጤቶች እያስገኘ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በምግብ ዋስትናና በተመጣጠነ የምግብ አቅርቦት ላሳዩት ርዕይ፣ የአመራር ቁርጠኝነት ከዓለም የምግብ እና የእርሻ ድርጅት (ፋኦ) የአግሪኮላ ሜዳልያ በጥር ወር 2016 ዓ.ም ያበረከተው ሽልማት ለምግብ ሉዓላዊነት ጥረት የተሰጠ እውቅና ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የኢትዮጵያ መንግስት ረሃብን ሙሉ በሙሉ ከማስቀረት ባለፈ የምግብ ሉዓላዊነትን በማረጋገጥ ብሔራዊ ብልጽግናን እውን ለማድረግ እየሰራ መሆኑን በሽልማቱ ወቅት ገልጸው ነበር። ኢትዮጵያ በርካታ ያልተነኩ ጥሬ ሃብቶች፣ ተስማሚ የአየር ንብረትና ለስራ ትጉ የሆነ ወጣት እንዳላት እና እነዚህን ሃብቶች ታሳቢ በማድረግ የታሪክ አውራ የሆነችውን ሀገር ልማት ወደፊት ለማራመድ የሚያስችሉ ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን አንስተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአንድ ወቅት የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት ለማስከበር ዋጋ እንደከፈልን ሁሉ ከምግብ ጥገኝነት ለመላቀቅ በትጋት መስራት እንደሚገባ ተናግረው ነበር። የምግብ ሉዓላዊነት፣ የቴክኖሎጂ ሉዓላዊነት፣ የበጀት ሉዓላዊነት፣ ታላቁን የሀገር ሉዓላዊነት በጽናት የሚያቆሙ ናቸው። እነዚህን የሉዓላዊነት ዘርፎች ለማስከበር አዲሱ ዓይነት አርበኝነት ያስፈልገናል። ይህም የብሔራዊነት አርበኝነት መሆኑንም ከዚህ ቀደም መናገራቸው ይታወቃል። የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) በተመሳሳይ ኢትዮጵያ በዓድዋ ጦርነት ያስመዘገበችውን አኩሪ ድል በዘመናዊ ግብርና የዜጎችን የምግብ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ እንደግመዋለን ሲሉ ገልጸው ነበር። በዓድዋ የዘመኑ ጀግኖች የሀገራቸውን የግዛት ሉዓላዊነት እንዳስከበሩት ሁሉ፣ የዚህ ዘመን ትውልድ ደግሞ ሌላ የራሱን ታሪክ መጻፍ እንዳለበት አንስተዋል። በዚህ ዘመን ደግሞ የዜጎችን የምግብ ሉዓላዊነት በማረጋገጥ ድሉን ለመድገም ትልቅ ተጋድሎ እያደረገች ነው ብለዋል። ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ኢትዮጵያ በተለያዩ አካባቢዎች ያሏትን ጸጋዎች እና ሀብቶች አሟጦ በመጠቀም ከተረጂነት ተላቆ ወደ ምርታማነት ለመሸጋገር የተለያዩ ስራዎችን እያከናወነች ትገኛለች። ከነዚህ ስራዎች መካከል አንዱ ከረድኤት ተቋማት ከሚደረግ የሰብዓዊ ድጋፍ ተላቆ ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተደረገ ያለው ጥረት ይገኝበታል። የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን የሀገርን ክብርና ሉዓላዊነት ለማስጠበቅ በራስ አቅም የሰብዓዊ ድጋፍን መሸፈን ይገባል በሚል እሳቤ አዲስ ስትራቴጂ ነደፎ እየሰራ ይገኛል። ይህ በስራ ላይ የዋለው ፖሊሲ የሀገርን ሉዓላዊ ነፃነት እና የዜጎችን ክብር በማስጠበቅ አደጋን በራስ አቅም ምላሽ በመስጠት የክምችትና የመጠባበቂያ ፈንድ አቅምን ማጎልበት የሚያስችል መሆኑን አስታወቋል። ለዚህም ሀገር አቀፍ የስትራቴጂክ መጠባበቂያ ክምችት አቅም ከ23 በመቶ ወደ 47 በመቶ የሚያሳድጉ ዘመናዊ የክምችት መጋዘኖች እየተገነቡ መሆኑን የኮሚሽኑ መረጃ ያመለክታል። ይህም የመፈጸም አቅምን በማሳደግ ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም መሸፈን በሚል ስኬታማ የአሰራር ማሻሻያ ሥርዓት መዘርጋቱን የሚያሳይ ነው። በ2016 ዓ.ም ጸድቆ ወደ ስራ የገባው የአደጋ ስጋት አመራር ፖሊሲ ዋነኛ ማጠንጠኛው በራስ አቅም የሰብዓዊ እርዳታን መሸፈን ላይ ያተኮረ ነው። የክልሎች ራስን የመቻል ስራዎች ፖሊሲው የውጭ እርዳታን ብቻ ሳይሆን ክልሎች ከፌደራል መንግስት ድጋፍ ተላቀው ራሳቸውን እንዲችሉ የማድረግ አቅም መገንባት ላይ መስራት እንደሚያስፈልግ የሚያመላክት ነው። በዚሁ መሰረት ድሬዳዋና አዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርን ጨምሮ ስድስት ክልሎች የሰብዓዊ ድጋፍ ጥያቄዎችን በራሳቸው መሸፈን የሚያስችል አቅም መፍጠራቸውን የኮሚሽኑ መረጃ ያመለክታል። በቀጣይም ሁሉም ክልሎች ራሳቸውን እንዲችሉ ጥረቶች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጿል። በኦሮሚያ ክልል ለመጠባበቂያ እህል ክምችት የሚውል ከ43 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ በመኸርና በበጋ ወራት እርሻ በማልማት 1 ነጥብ 7 ሚሊየን ኩንታል ምርት ለማግኘት እየተሰራ መሆኑን የቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ መረጃ ያመለክታል። በክልሉ ከማኅበረሰቡ የቆየ የመረዳዳት እሴት ተቀድቶ በክልሉ "ቡሳ ጎኖፋ ኦሮሚያ" በሚል ስያሜ በተቋም ደረጃ ተቋቁሞና ሕጋዊ እውቅና አግኝቶ ሰብዓዊ ድጋፍን በራስ አቅም ለመሸፈን እየሰራ ይገኛል። እየተከናወነ የሚገኘው የእርሻ ሥራ ክልሉ አሁን ላይ ያለውን 100 ሺህ ኩንታል የመጠባበቂያ እህል ክምችት ወደ 1 ነጥብ 8 ሚሊየን ኩንታል የሚያሳድግ መሆኑንም ተመላክቷል። በክልሉ የምርት ማከማቻ መጋዘኖችን በሕዝብ ተሳትፎ በክልሉ በሚገኙ 21 ዞኖችና በተመረጡ ስምንት ከተሞች ላይ ለመገንባት የዝግጅት ሥራዎች ተጠናቀው ወደ ስራ ተገብቷል። በአማራ ክልል ከተረጅነት ለመላቀቅና እርዳታን በራስ አቅም ለመሸፈን በ36 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ለመጠባበቂያ እህል ክምችት የሚውል ሰብል ለማልማት ታቅዶ ወደ ተግባር መገባቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ መረጃ ያመለክታል። በክልሉ በ2016/17 ምርት ዘመን ልማቱን በ36 ሺህ ሄክታር መሬት ላይ ለማካሄድ ታቅዶ እስካሁን ከ27 ሺህ 700 ሄክታር የሚበልጥ መሬት በመለየት ወደ ተግባር መግባቱን ቢሮው ገልጿል። ለምርት ማሳደጊያ የሚውል 1 ሺህ 914 ኩንታል ማዳበሪያና 1 ሺህ 154 ኩንታል ምርጥ ዘር ቀርቦ ጥቅም ላይ እየዋለ እንደሚገኝም እንዲሁ። በራስ አቅም የመጠባበቂያ እህል በማምረት ዕርዳታን ሳይጠበቅ ለችግር ለሚጋለጡ ዜጎች ተደራሽ በማድረግ ክልሉን ከተረጅነት ለማላቀቅ የተያዘው ግብ እንዲሳካ በትኩረት እየሰራ መሆኑንም ቢሮው አመልክቷል። ሌላኛው የሰብዓዊ ድጋፍን በራስ የመሸፈን አቅም ጥረት ማሳያ የሲዳማ ክልል ነው። በክልሉ ለአደጋ ጊዜ መጠባበቂያ የሚሆን የምግብ ሰብል ክምችት በወል መሬት የማልማት ስራ በስፋት እየተከናወነ እንደሚገኝ ተጠቁማለ። በዚህም በክልሉ በመኸር እርሻ 800 ሄክታር የወል መሬት ለአደጋ ጊዜ መጠባበቂያ እንዲሆኑ በተለያዩ ሰብሎች መልመካቱን መረጃዎች ያመለክታሉ። የሲዳማ ክልል የተረጂነት ጉዳይ የሉአላዊነት ጉዳይ መሆኑን ከግምት በማስገባት በራስ አቅም የመጠባበቂያ ምግብ ክምችት ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑም ተመላክቷል። በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልም በተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ሰብአዊ እርዳታን በራስ አቅም ለመሸፈን የክልሉ መንግስት የተለያዩ የልማት ስራዎችን እያከናወነ ይገኛል። የክልሉ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን በራሱ እያለማ ያለው የሰብል ማሳ የዚሁ ስራ ማሳያ ነው። ኮሚሽኑ በዘንድሮው ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ በ56 ሄክታር ማሳ ላይ በቆሎ፣ ማሽላ፣ አኩሪ አተር እና ሌሎች ሰብሎችን እያለማ እንደሚገኝ ገልጿል። በክልሉ ሁሉም ወረዳዎች በምግብ ራስን መቻል እና ሰብአዊ ድጋፍን በራስ አቅም መሸፈን በሚል መርህ የተለያዩ ሰብሎች እየለሙ መሆኑንም አመልክቷል። ሌላኛው በተሞክሮነት የሚጠቀስ ስራ እያከናወነ የሚገኘው ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ነው። ክልሉ ለድንገተኛ የተፈጥሮ አደጋ በራስ አቅም ምላሽ መስጠት የሚያስችል አቅም ለመገንባት ትኩረት አድርጎ እየሰራ ይገኛል። እምቅ የልማት አቅምን በመጠቀምና ምርታማነትን በማሳደግ በምግብ ራስን መቻል የክልሉ መንግስት ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫው አድርጎታል። በዚህም በቀጣይ ሁለት ዓመታት በክልሉ የሴፍቲኔት መርህግብር ተጠቃሚዎችን ወደ ዘላቂ ልማት በማሸጋገር ከተረጂነት የሚወጡበት ልዩ ዕቅድ ተዘጋጅቶ ወደ ሥራ ተገብቷል። አረንጓዴ አሻራ እና የሌማት ትሩፋትን በማስተሳሰር እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት በክልሉ ከተረጂነት ወጥቶ ራስን ለመቻል እየተደረገ ያለው ጥረት ማሳያ ናቸው። ሌሎች ክልሎችም በራሳቸው አቅም የሰብዓዊ ድጋፍ ለመሸፈን በመስራት ላይ ይገኛሉ። ተግባራቱ ከተረጅነት ለመላቀቅና እርዳታን በራስ አቅም ለመሸፈን እየተደረገ ያለውን የባህል ለውጥ በግልጽ የሚያሳዩ ናቸው። የመውጫ ሀሳብ በኢትዮጵያ ሰብዓዊ እርዳታ የሚሹ ወገኖችን ተደራሽ ማድረግ የሚያስችል አሁናዊ በቂ የሰብዓዊ ድጋፍ ክምችትና ዝግጅት መኖሩን የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽነር አምባሳደር ሽፈራው ተክለማርያም (ዶ/ር) ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ገልጸዋል። መንግስት በተፈጥሯዊ እና ሰው ሰራሽ ምክንያቶች የሚከሰቱ አደጋዎችን መቋቋም የሚያስችሉ ሀገራዊ ፖሊሲና ስትራቴጂ ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አመልክተዋል። በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች የሚከሰቱ አደጋ ስጋቶችን ለመቋቋምና ድጋፍ የሚሹ ወገኖችን ለመድረስ ማህበረሰቡ እርስ በርስ የሚተጋገዝበትን ስርዓት ለማጠናከር ትኩረት መደረጉንም እንዲሁ። በሌላ በኩል የመጠባበቂያ ክምችት በመፍጠር ሰብዓዊ ድጋፍ በራስ አቅም በዘላቂነት ተደራሽ ማድረግ የሚያስችል ሀገራዊ አቅም ለመፍጠር ወደ ስራ መገባቱንም ኮሚሽነሩ አንስተዋል። በዚህም ካሳለፍነው ክረምት ጀምሮ እስከ በ2017/2018 የምርት ዘመን 253 ሺህ ሄክታር መሬት በማረስ 2 ሚሊየን ሜትሪክ ቶን ወይም 20 ሚለዮን ኩንታል ምርት በማምረት መጠባበቂያ ክምችት ለመያዝ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። እስከ አሁንም 108 ሺህ ሄክታር መሬት መታረሱን ገልፀው፤ ይህም የዕቅዱን 43 ከመቶ ይሸፍናል ነው ያሉት። ዕቅዱን ዕውን በማድረግ እንደ ሀገር ሙሉ የመጠባበቂያ ክምችት በመያዝ በፌደራልና በክልል ደረጃ ቀዳሚ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን በመግለጽ። በሀገር ደረጃ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ምክንያት የሚያጋጥሙ ችግሮችን በራስ አቅም ምላሽ ለመስጠት አቅም የሚፈጥሩ ናቸው። ኢትዮጵያ ከ26 ሀገራት ለመጡ ከ1 ነጥብ 1 ሚሊዮን በላይ ስደተኞችና ጥገኝነት ጠያቂዎችን አስጠልላ ከለላና የተለያዩ መሠረታዊ አገልግሎቶችን በመስጠት ላይ ትገኛለች። እንደ የስደተኞች እና ተመላሾች አገልግሎት መረጃ ከሆነ በስደተኞች ስም የመጣ ማንኛውም ድጋፍ ለታለመለት ዓላማመዋሉን የመከታተልና የመቆጣጠር ኃላፊነት ያለበት በመሆኑ ከዋና መሥሪያ ቤት ጀምሮ የስደተኛ ማዕከላት ድረስ የክትትልና ቁጥጥር ሥርዓት ዘርግቶ እየሠራ ይገኛል። በዚህም መሠረት ሩሲያ የደቡብ ሱዳንን የእርስ በርስ ጦርነት ተከትሎ ወደ ኢትዮጵያ የገቡና በጋምቤላ ክልል ለተጠለሉ የደቡብ ሱዳን ስደተኞችና ጥገኝነት ጠያቂዎች በዓለም የምግብ ፕሮግራም (WFP) በኩል 1 ሺህ 632 ነጥብ 4 ሜትሪክ ቶን የስንዴ ድጋፍ ትናንት አድጋለች። የስደተኞች ሰብዓዊ ድጋፍ ከተለያዩ መንግስታትና ዓለም አቀፍ ተቋማት በሚደረግ ድጋፍ በዓለም የምግብ ፕሮግራም በኩል ሲከናወን ቆይቷል፤ የአሁኑ ድጋፍም የተደረገው ለተመሳሳይ ዓላማ እንደሆነም አገልግሎቱ አመልክቷል። ኢትዮጵያ የአጋር አካላት ድጋፍ መቀዛቀዙን ተከትሎ ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ በኢትዮጵያ ለሚገኙ የተለያዩ አገራት ስደተኞች የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ በተደጋጋሚ ጊዜ ጥሪ ማቅረቧ ይታወቃል። ዓለም አቀፍ ረጂ አካላትም ስደተኞች ሰብዓዊ መብታቸው ተጠብቆ መሠረታዊ አቅርቦት እንዲያገኙ ቀጣይነት ያለው ድጋፍ ማድረግ እንዳለባቸውም ስትገልጽ ቆይታለች። በሀገር ደረጃ እየተደረጉ የምግብ ሉዓላዊነትን ለማረጋገጥ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ምክንያት የሚያጋጥሙ ችግሮችን በራስ አቅም ምላሽ ለመስጠት አቅም የሚፈጥሩ ናቸው። ኮሚሽኑ የሰብዓዊ አገልግሎት፣ ዘላቂ ልማትና የሰላም ጥምረትን በማረጋገጥ ዕውቀት መር በራስ አቅም አደጋን ምላሽ የሚሰጥ ተቋም ለመገንባት የማሻሻያ እርምጃዎችን ወስዷል። የራስ አቅም ግንባታው በአጠቃላይ በኢትዮጵያ በ2030 ዓ.ም ለአደጋ ስጋት የማይበገር ማህበረሰብን ለመገንባት እቅድ ቁልፍ ሚና ይጫወታል። ሀገራዊ ትልሙ ኢትዮጵያን ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ለተሟላ ሀገራዊ ክብር፣ ነጻነት እና ሉዓላዊነት የሚያሸጋግር መልካም ጅማሮ ነው።
የኃይል ልማት ለቀጣናዊ ትስስር
Jan 3, 2025 253
ወዳጅ ማብዛትና አጋር ማበራከት የኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ መርህ ነው። ፖሊሲዋ ለጎረቤት አገራት ቅድሚያና ልዩ ትኩረት ይሰጣል። ለቀጣናዊ ትስስር፣ የጋራ እድገትና ተጠቃሚነት ትኩረት የዲፕሎማሲዋ አስኳል ነው። ቀጣናዊ ትስስሩን ዕውን ለማድረግ ከፊት ተሰላፊ ሀገር ናት። በዚህም በትብብር ዲፕሎማሲና የህዝብ ለህዝብ ትስስርን በማጎልበት የጋራ ልማትን ማረጋገጥ ሰርክ ታነሳለች። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) የኢትዮጵያ የሁልጊዜም ፍላጎት በቀጣናዊ ትብብር ከጎረቤት አገራት ሰላም እንዲመጣ በትብብር መሥራት፣ አብሮ ማደግና በጋራ መበልጸግ መሆኑንም በተደጋጋሚ ሲገልጹ ይደመጣል። ከቀጣናው ሀገራት ትብብር መስኮች አንዱ በኃይል መሰረተ ልማት መተሳሰር መሆኑ እሙን ነው። ኢትዮጵያ የምሥራቅ አፍሪካ የውሃ ማማ መባሏ በምክንያት ነው። ከወንዞቿ በዓመት 124 ቢሊዮን ኪዩብ ሜትር እንዲሁም ከከርሰ ምድር ከ36 እስከ 40 ቢሊዮን ኪዩብ ሜትር ውሃ ሀብት እንዳላት መረጃዎች ያሳያሉ። ይህ የውሃ ሀብቷ ደግሞ ታዳሽ ኃይል ግንባታ አይተኬ ሚና አለው። የውሃ ሀብቷ ከፀሐይ፣ በነፋስ እና በጂኦ-ተርማል የኃይል አማራጮች ጋር ተዳምሮ ከ300 እስከ 400 ጊጋ ዋት ኃይል የማመንጨት አቅም አላት። በ10 ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅዷ ኢትዮጵያ የምታመነጨውን የኃይል መጠን አሁን ካለበት 4 ሺህ 818 ሜጋ ዋት ወደ 17 ሺህ ሜጋ ዋት ለማሳደግ ግብ ተቀምጧል። የተሻሻለው የኢነርጂ ፖሊሲዋም ሀገራዊ፣ ቀጣናዊና ዓለም አቀፍ ነባራዊ ዕውነታ መሰረት ያደረገ እና ጎረቤት ሀገራትን በኃይል መሰረተ ልማት ለማስተሳሰር ያለመ ነው። በ10 ዓመት መሪ ዕቅዱ መሰረት ለጎረቤት አገራት እየቀረበ ያለውን 2 ሺህ 803 ጊጋ ዋት ሰዓት ሽያጭ ወደ 7 ሺህ 184 ጊጋ ዋት ሰዓት ለማሳደግ ውጥን ተይዟል። ኢትዮጵያ በአውሮፓዊያኑ አቆጣጠር ለጅቡቲ በ2011፣ ለሱዳን በ2012፣ ለኬንያ በ2022 እንድሁም በቅርብ ጊዜ ለታንዛኒያ ኤሌክትሪክ ኃይል ማቅረብ ጀምራለች። የኃይል ሽያጩ በየዓመቱ እያደገ መጥቶ በ2015 በጀት ዓመት ወደ 101 ነጥብ 2 ሚሊዮን ዶላር እንዳደገ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል መረጃ ያመለክታል። የቀጣናው ከፍተኛ ኤሌክትሪክ ኃይል ማስተላለፊያ (ሃይዌይ) ፕሮጀክት የመጀመሪያው ምዕራፍ ኢትዮጵያና ኬንያን፤ በቅርብ ወደ አገልግሎት የገባው ሁለተኛው ምዕራፍ ደግሞ ኬንያንና ታንዛኒያ አስተሳስሯል። የኃይል አቅርቦቱ ከሶስቱ ሀገራት ባሻገር ለቀጣናው ሌሎች ሀገራትም ትስስር መሰረት ጥሏል። ኢትዮጵያ በቀጣይ ለደቡብ ሱዳን፣ ሩዋንዳ፣ ብሩንዲና ሌሎች አገራት የኤሌክትሪክ ኃይል የመሸጥ ዕቅድ ይዛለች። ወደ ደቡብ ሱዳን የሚደረገው ኤሌክትሪክ መስመር ዝርጋታ በሂደት ላይ መሆኑ ይታወቃል። ኢትዮጵያ ቀጣናውን በኃይል አቅርቦት ረገድ የጋራ ልማትን መሰረት ያደረገ በመሆኑ በተመጣጣኝ ዋጋ ነው የምታቀርበው። ሀገራቱ ከኢትዮጵያ የሚገዙት የኃይል አቅርቦት ደግሞ ለአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፋቸው እመርታ ፈጥሯል። ይህ ደግሞ ወዲህ የጎረቤት ሀገራትን ቅድሚያ የሰጠውን ፖሊሲዋን በተግበር የገለጠ ነው፤ ወዲያ ደግሞ ከውጭ ምንዛሬ ግኝት ባሻገር ለቀጣናዊ ትስስርን ለማጎልበት አይተኬ ሚና ይኖረዋል። ይህ ደግሞ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ነጻ የንግድ ቀጣና ስምምነት እንዲሁም ለአፍሪካ አጀንዳ 2063 ዕውን መሆን በኢነርጂ ዘርፍ ያላትን ቀዳሚ ስፍራ ያረጋገጣል። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለቀጣናዊ ትስስር ሌላው በረከት ነው። ግንባታው በመጠናቀቂያ ምዕራፍ ላይ የሚገኘው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ገጸ ብዙ ፕሮጀክት ነው። ከኢትዮጵያ አልፎ ለአፍሪካ ልዩ በረከት ይዞ የመጣ፤ የታዳሽ ኃይል ልማት አብነት ነው። በዐባይ ወንዝ የዘመናትን ብክነትና ቁጭት የቋጨ ነው። በሌላ ጎኑ በራስ አቅም ብቻ የተጠናቀቀ ነው። በአፍሪካ ግዙፉ የኃይል ማመንጫ ግድብና ለቀጣናው ሀገራት ትስስር መልህቅ ስለሆነም ፓን አፍሪካዊ ፕሮጀክት ያሰኘዋል። ኃይል ማመንጨት የጀመረው ግድቡ በዓመት 5 ሺህ 150 ሜጋ ዋት የኤሌክትሪክ ኃይል ያመነጫል። እስካሁን በግድቡ አራት ተርባይኖች ኃይል እያመነጩ ነው። ግድቡ ተጠናቆ የሁሉም ተርባይኖች ስራ ተጠናቆ ወደ ምርት ሲገባ ሀገራዊ የኃይል አቅምን 130 በመቶ ያሳድጋል። ይህ ደግሞ አንድምታም ብዙ ነው። ሀገራዊ የኃይል ፍላጎትን ከመሸፈን አልፎ በቀጣነው ሀገራት ተደራሽ በመሆን የኢትዮጵያን አፍሪካን የማስተሳሰር ቀንዲልነት ያጎላል። ለዚህ ነው ግድቡ ለቀጣናው ሀገራት ገጸ በረከት ነው የሚያሰኘው። በርግጥ ከሕዳሴው ግድብ ባሻገር ሌላው ከአፍሪካ ግዙፍ ፕሮጀክቶች አንዱ የሆነው የኮይሻ ኃይል ማመንጫም ለቀጣናዊ ትስስር መፋጠን ሌላው እድል ነው። በጥቅሉ ኢትዮጵያ ለጎረቤት አገራት የምታቀርበው የኤሌክትሪክ ኃይል የሀገራት ኢኮኖሚ ትብብር የሚያጠናክር እና የኢትዮጵያን የመሰረተ ልማት የማስተሳሰር ጽኑ ፍላጎት ማሳያ ነው። በተጨማሪም በክቀጣናው ዘላቂ የኤሌክትሪክ ገበያ ልማትን ለማረጋገጥ የሚያስችል ክፍለ አሕጉራዊ ጥረት ነው። ጥረቱ የምሥራቅ አፍሪካ የሃይል ቋት (The Eastern Africa Power Pool-EAPP) በቀጣናው ሀገራት መካከል ድንበር ተሻጋሪ የሃይል ንግድ እና የሃይል መስመር ትስስርን ለማሳለጥ እኤአ በ2005 የተቋቋመ ተቋም ግብ እውን ከማድረግ ባለፈ አሕጉራዊ ምጣኔ ሃብታዊ ትስሰርን የሚያፋጥን ነው።
የቤተ መንግሥቱ ነገ…
Dec 28, 2024 5949
(እንደ ፈረንሳዩ ቨርሳይ፤ እንደ ሩስያው ፒተርሆፍ) በአየለ ያረጋል ማሟሻ… ከምድራችን ግንባር ቀደም ተናፋቂ አብያተ መንግሥታት መካከል ቬርሳይ አንዱ ነው። ከፈረንሳይ ርዕሰ መዲና ፓሪስ በስተምዕራብ ወጣ ብሎ ይገኛል። ‘የሩስያዋ ቨርሳይ’ የሚሰኘው በቅዱስ ፒተርስበርግ ከተማ የሚገኘው ፒተርሆፍ አብያተ መንግስሥታት ሌላው ነው። ሁለቱም አብያተ መንግሥታት ዛሬ አብያተ-መዘክሮች ሆነዋል። ተፈጥሮ፣ ታሪክና ቅርስ የተዛነቀባቸው የዕልፍ አዕላፍ ቱሪስቶች መነሀሪያ ናቸው። በአንድ ስፍራ የሀገር መልክ እና ልክ የተገለጠባቸው። የአዲስ አበባው ብሔራዊ ቤተ መንግሥትም የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ‘የአፍሪካ ቨርሳይ’ መባሉ አይቀሬ ነው። ለምን ቢሉ ዘመንና ስፍራ ቢለያቸውም የታሪክ ዑደታቸው፤ የዘመን ቀለማቸው፣ የብዝሃ ቅርስ ባለቤትነታቸው ያመሳስላቸዋልና! የፈረንሳይ ንጉሳዊያን ቤተሰቦች በፈረንሳይ አብዮት ከቨርሳይ ቤተ-መንግሥት ተባረዋል። የሩስያ ዘውዳዊ ስርዓት (ፃሮች ስርዓት) በኮሚኒስቶች አብዮት ከፒተርሆፍ ቤተ-መንግሥት ላይመለስ ተገርስሷል። በተመሳሳይ የኢትዮጵያ ሠለሞናዊ ዘውዳዊ ስርዓት ከብሔራዊ ቤተ መንግሥት ፍጻሜውን አግኝቷል!! ቨርሳይ ቤተ መንግሥት ለፈረንሳይ ከአራት ምዕተ ዓመታት በፊት ነው። ቨርሳይ ላይ የፈረንሳይ ግዛተ አፄ ንጉሥ ሉዊ 13ኛ ለአዳኞች ዕልፍኝ ገነባ። ልጁ ንጉሥ ሉዊ 14ኛ ደግሞ የቨርሳይ ቤተ መንግሥትን መሰረተ። በጊዜው ቅንጦት ተብሎ ፈረንሳያዊያን ‘እግዚኦ’ አሉ። በፈረንጆቹ 1661 የነገሰው ንጉሥ ሉዊ 14ኛ ግን ለመንግስቱ ክብር ዕፁብ ድንቅ የሆነውን የቨርሳይ ቤተ መንግሥቱን አነፀ። ሌሎች ነገሥታትም አሻራቸውን እያከሉ ኖሩበት። በተለያዩ አገልግሎቶችን አስተናግዶ፣ የፈረንሳይን አብዮት ጨምሮ መልከ ብዙ ታሪካዊ ሁነቶችን አስተናግዶ ዘመናት ተሻገረ። በጎርጎሬሳዊያኑ 1837 በወቅቱ ንጉስ ሉዊ ፕሊፕ የቨርሳይ ቤተ-መንግሥት ወደ ቤተ መዘክርነት ተለወጠ። እነሆ የቀድሞው ቨርሳይ ቤተ-መንግሥት ከነግርማ ሞገሱ 400 ዓመታትን ዘለለ። ዛሬ ከዓለማችን ምርጥና ዝነኛው ቤተ መዘክሮች አንዱ ነው። በአውሮፓዊያኑ ዘመን ቀመር በ1979 ዓ.ም ከጎንደሩ የፋሲል ቤተ መንግሥት ጋር በዩኔሰኮ የዓለም ቅርስነት ተመዘግቧል። በፈረንሳይ ባህልና ቅርስ ሚኒስቴር ስር ይተዳደራል። የቨርሳይ ቤተ-መዘክር ኪነ ሕንጻ ብቻ አይደለም። ስነ ውበት፣ ኪነ ሕንጻና ኪነ ጥበብ ጥግ የሚነበብበት ከ800 ሄክታር በላይ የሚሸፍን ሠፊ ምድረ ግቢ ነው። ቤተ መንግሥቱ 63 ሺህ 154 ካሬ ሜትር ላይ ያረፉ 2 ሺህ 300 ቤቶች አቅፏል። የንጉስ ማደሪያ ቤት፣ ቋሚ ዐውደ ርዕዮች፣ ፋፏቴዎች፣ ሙዚየም፣ አረንጓዴ ስፍራ፣ የፈረሰኞች አካዳሚ፣ የገበያ ስፍራ፣ መናፈሻዎች፣ የቴኒስ መጫዎቻ ቦታ እና ሌሎች የተለያዩ ክዋኔ ስፍራዎችን በውስጡ አምቆ ይዟል። ቨርሳይ በጌጣጌጦቹ፣ በቅርፃ ቅርጾቹ፣ በስዕል ጥበቦቹ ሁሉ አጃይብ የሚያሰኝ ስፍራ ነው። ቨርሳይ ቤተ መንግሥት ቨርሳይ የፈረንሳይ የኩራት ትዕምርት ነው። የዓለማችን ቀዳሚዋ የቱሪስት መዳረሻ በሆነችው ፈረንሳይ ከተወዳጅና ተመራጭ የሀገሪቷ የቱሪስት መዳረሻዎች መካከል ቨርሳይ አንዱ ነው። በየዓመቱ 15 ሚሊዮን ሕዝብ ይጎበኘዋል። ይህ ማለት ከምስራቅ አፍሪካዋ ሩዋንዳ ጠቅላላ ሕዝብ ቁጥር የበለጠ ጎብኚ ቨርሳይ ላይ በየዓመቱ ይጎርፋል ማለት ነው። ከ2 ሺህ 500 በላይ ቀጥተኛ፣ ከ10 ሺህ በላይ ተዘዋዋሪ ስራ ዕድል ፈጥሯል። ቨርሳይን ጨምሮ ፈረንሳይ በዓመት እስከ መቶ ሚሊዮን ዶላር ገቢ ታመነጫለች- በትናንት ታሪክና ቅርሷ። ፒተርሆፍ ቤተ-መንግሥት የዘመናዊት ሩስያ መስራች ታላቁ ፒተር ቀዳሚ በንጉሥ ሉዊ 14ኛ ዘመን ወደ ፈረንሳይ ተሻገረ። በቨርሳይ ቤተ-መንግሥትን በክብር ተስተናገደ። በተመለከተው ትዕይንት ተደነቀ፤ ተገረመ። የፒተርሆፍ ቤተ መንግሥትን እንዲያንጽ ምክንያት ሆነው። ፒተርሆፍ ቤተ መንግሥት በቅዱስ ፒተርስበርግ ከተማ ይገኛል። ቀዳማዊ ፒተር በአውሮፓዊያኑ 1709 ታነጸ። ብዙሃኑ ፒተርሆፍን ‘የሩስያው ቨርሳይ’ ይሉታል። የክረምቱ ቤተ መንግሥትም ይሰኛል። የሩስያ ታሪክ፣ ጥበብና ቅርስ ማዕከል ነው። የሩስያ ጣሪያ አለባ ቤተ መዘክር(Open air musuem) በምትሰኘዋ ቅዱስ ፒተርስበርግ ከተማ ከሚገኙ ቀዳሚ የቱሪስት መነሃሪዎች መካከል አንዱ ፒተርሆፍ ነው። ፒተርሆፍ ቤተ መንግሥት በ3 ሺህ 934 ሄክታር ላይ ያረፈው ፒተርሆፍ በውስጡ ግዙፍ ቤተ መንግሥት፣ ዕውቁ የሳምሶን ፋውንቴን፣ አረንጓዴ ስፍራዎች፣ ፏፏቴዎች፣ መናፈሻዎች፣ ማራኪ ኪነ ሕንጻዎች፣ ጥንታዊ ስዕላት፣ ቤተ መዘከር እና ሌሎች የከበሩ ቅርሶችን ይዟል። የዚህ ጽሁፍ ጸሀፊ ፒተርሆፍን ምድረ ግቢ የማየት ዕድል ያገኘሁ ሲሆን ታሪክ፣ ቅርስና ተፈጥሮ እንዴት መሳ ለመሳ ተሰናስነው ሀሴትን እንደሚያላብሱ ታዝቤያለሁ። ሩስያዎች ታሪክና ቅርሳቸውን እንዴት ለዘመናት ጠብቀው እንጀራ እያበሰሉበት እንዳለም እንዲሁ። በአውሮፓዊያኑ በ1990 በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት ተመዝግቧል። በየዓመቱ በአማካይ ስድስት ሚሊዮን ቱሪስቶች ይጎበኙታል። ከቅዱስ ፒተርስበርግ ብቻ ሳይሆን ከመላዋ ሩስያ ምርጥ ቱሪስት መዳረሻዎች መካከ አንዱ ነው። ፒተርሆፍ ቤተ መንግሥት በኢትዮ-ሩስያ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የራሱ ታሪካዊ አሻራ እንዳለው መጥቀስ ተገቢ ነው። ይሄውም ከአድዋ ድል አንድ ዓመት ቀደም ብሎ በ1887 ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ በፊታውራሪ ዳምጠው ከተማ(የራስ ደስታ አባት) የተመራ የኢትዮጵያ ልዑክ ሩስያን ሲረግጥ ደማቅ አቀባበል የተደረገለት በፒተርሆፍ ቤተ መንግሥት ነበር። በፊታውራሪ ዳምጠው ከተማ ልዑክ በፒተርሆፍ ቤተ መንግሥት ፊታውራሪ ዳምጠው ከተማ ከአጼ ምኒልክና ከእቴጌ ጣይቱ የተላኩ ስጦታዎችን ለንጉስ(ጻር) ኒኮላስ ዳግማዊ እና ለባለቤታቸው ቀዳማዊት አሌክሳንድራ ያስረከቡት ፒተርሆፍ ቤተ መንግሥት ነበር። ከሩስያ ሲመለሱም ለአድዋ ጦርነት ስንቅ የሆኑ የጦር መሳሪያዎች እና የቀይ መስቀል አባላትን አስከትለው ተመልሰዋል። ይህም የሩስያው ቨርሳይ(ፒተርሆፍ) ከኢትዮጵያ ጋር የሚያስተሳስራት ሌላ ታሪካዊ ገመድ እንዳለ ያረጋግጣል። ብሔራዊ ቤተ መንግሥት ለኢትዮጵያ የምድረ ቀደምቷ ሀገር ኢትዮጵያ ብሄራዊ ቤተ መንግስት የአአፄ ኅይለሥላሴን 25ኛ ዓመት(የብር ኢዮቬልዮ) የንግሥና ክብረ በዓል ምክንያት በማድረግ የተገነባ ነው። በ1953 ዓ.ም የመፈንቀለ መንግሥት ሙከራ በኋላ ንጉሠ ነገሥቱ ገነተ ልዑልን(አሁን አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) ለቀው እስከ ሕልፈተ ሕይወታቸው ድረስ መኖሪያቸው ይሄው ቤተ-መንግሥት ነበር። በደርግ ዘመን ወደ ‘ብሔራዊ ቤተ መንግሥት’ነት ስሙ ከመለወጡ በፊት ‘ኢዮቬልዮ ቤተ መንግሥት’ እየተባለ ሲጠራ ቆይትል። ከታላቁ ወይም ከዳግማዊ ምኒልክ ቤተ መንግሥት ጋር በማነጻጸር ደግሞ የታችኛው ቤተ-መንግሥትም ይባል ነበር። በደርግ ዘመን ፋውንቴኖችና ሌሎች መዝናኛ ስፍራዎች ተገንብተውለታል። በኢሕአዴግ መንግሥት ደግሞ የርዕሰ ብሔሮች መኖሪያና እንግዳ መቀበያ ሆኖ አገልሏል። ሀገራዊ የክብር ክዋኔዎች መስተናገጃ ነው። የእንግሊዟን ንግስት ቪክቶሪያ ጨምሮ በርካቶች የዓለማችን ዕውቅና ዝነኛ መሪዎች ተስተናግደውበታል። በዚህ ቤተ መንግሥት የንግስቷ እልፍኝ የተባለ ክፍልም እንዳለ መረጃዎች ያሳያሉ። በኢጣሊያናዊው የኪነ ሕንፃ ባለሙያ ራፋዔል ፔትሮን የተነደፈው ቤተ መንግሥቱ፤ የኢትዮጵያን ባህላዊ የኪነ ሕንፃ እሴት እና የዘመናዊ ኪነ ህንፃ ለዛ አጣምሮ የያዘ እንደሆነ ይነገርለታል። አፄ ኅይለሥላሴ በብሔራዊ ቤተ መንግሥት አፄ ሃይለሥላሴ (ያኔ ልዑል አልጋወራሽ ራስ ተፈሪ) በፈረንጆቹ 1924 የተመረጡ 39 አባላትን ያቀፈ ልዑክ መርተው መካከለኛው ምሥራቅና አውሮፓን መጎብኘታቸው ይታወሳል። በአውሮፓ ሀገራትም የዓለማችን ምርጥ አብያተ መንግስታትና ታሪካዊ ስፍራዎችን ተመልክተዋል። ራስ ተፈሪ ከጎበኟቸውና ቀልባቸውን ከሳባቸው የፈረንሳይ ታሪካዊው ስፍራዎች መካከል የቬርሳይ ቤተ መንግሥት ይገኝበታል። አልጋ ወራሹ የመጀመሪያ የውጭ ሀገር ጉዞ በሆነው በዚሁ ጉብኝት ወቅት ከፈረንሳይ መሪዎች ጋር ተወያይተዋል። በውይይታቸውም ኢትዮጵያ የባሕር በር ባለቤትነት ዋስትና ጉዳይ ቀዳሚው አጀንዳ እንደነበር ታሪክ ያወሳል። አስገራሚው ነገር ከአንድ ምዕተ ዓመት በኋላ በቅርቡ በብሔራዊ ቤተ መንግሥት ንግግር ያደረጉት የፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት አማኑኤል ማክሮን ‘ኢትዮጵያ የባህር መውጫ በር ያስፈልጋታል የሚለው ንግግር ታሪካዊ ግጥምጥሞሽ ያሰኘዋል። የቤተ መንግስቱ ስፋት፣ ዘመናዊነትና ኪነ ሕንፃ ውበት ብቻ ሳይሆን በውስጡ የያዛቸው ቅርሶችና ያስተናገዳቸው ታሪኮች የተለዬ መልክ እንዲኖረው ያደርጋል። የዘመናዊ የኢትዮጵያ ታሪክ መነሻ ሀብቶችን አቅፏል። የቤተ መንግስቱ መገኛ ስፍራ የአዲስ አበባ ከተማ የተወጠነበት አስካል በመሆኑ ከሌሎች ታሪካዊ ስፍራዎች ሌላው ልዩ ገጽታው ያላብሰዋል። ቤተ መንግሥቱ የኢትዮጵያ ብዝሃ ታሪክ ባለቤትነትና የምንጊዜም ነጻ ሀገርነት ማሳያ ትዕምርትም ነው። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከአራት ዓመት በፊት ቤተ መንግስቱንና ቅርሶቹን እያስጎበኙ፤ ያልተገለጠው ሀብት እሴት ተጨምሮበት ለጎብኚዎች ክፍት የማድረግ ሃሳባቸውን ማጋራታቸው ይታወሳል። ቤተ መንግስቱ ታድሶ ለሕዝብ ክፍት ቢደረግ ለሀገር ምን ያህል በረከት ይዞ እንደሚመጣ የሰጡት ማብራሪያም የብዙሃኑን ቀልብ የሳበ ነበር። ብሔራዊ ቤተ መንግሥት ከፍልውሃ፤ ከፊንፊኔ ባሕል አዳራሽ፣ ከግዮን ሆቴል እና ከአፍሪካ አዳራሽ ጋር የተያያዘ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት የቤተ መንግሥት ምድረ ግቢ ከፍልውሃና ፊንፊኔ አዳራሽ ጋር ተዳምሮ ከ70 እስከ 80 ሄክታር ስፋት አለው። በትልልቅ ዛፎች ውብ ሀመልማላዊ ገጽታ የተላበሰ፤ ድንቅና ብርቅ ታሪካዊ ሀብቶች ይገኙበታል። “መሀል ከተማ ላይ ትልልቅ ዛፎች ያሉት፣ በጣም የሚገራርሙ ታሪካዊ ሀብቶችን የያዘ ስለሆነ ሙሉ ስራ ከተሰራለት በምንም መመዘኛ በየትኛውም የዓለም ክፍል ካሉ ካፒታል ሲቲዎች ሊወዳደር የሚያስችል በቃት አለው” ነበር ያሉት። ለአብነትም በቤተ መንግስቱ ውስጥ የሚገኙ መኪናዎችን የ’ካር ሙዚዬም’ ገንብቶ ለጎብኚዎች ክፍት ቢደረግ ኢትዮጵያ ምን ያህል ተጠቃሚ እንደምትሆን ጠቁመው ነበር። “እነዚህ መኪኖች እኛ ከተማም ይሁን ሌላ ዓለም በቀላሉ የሚታዩ አይደሉም። አይታዩም፤ ብርቅ ናቸው። እነዚህን በጣም ውብ በሆነ መንገድ የመኪና ኤግዚቪሽን ብንሰራ በጣም ብዙ ሰው መጥቶ ያያቸዋል። አንደኛ የንጉሥ መኪና ናቸው። ሁለተኛ አፍሪካ ውስጥ የዛሬ 50 ዓመት 60 ዓመት በዚህ ደረጃ የደረጀ ሀብት እንደነበር የሚያሳይ ነው። … አፍሪካ ውስጥ ኢትዮጵያ ውስጥ ጥንታዊ ታሪክ ያላት ከ50 ዓመት በፊት እንደዚህ አይነት ውቅር የደረጀ መንግስቷ የሚንቀሳቀስ ሀገር ናተ የሚለው ቀላል ትርጉም የሚሰጠው አይደለም” ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስላስደመመቻቸው ‘አምፊካር’ ስለተሰኘችዋ ተሽከርካሪ ሲያብራሩም “በጣም ከገረመኝ ነገር አምፊካር የምትባለውዋ መኪና ናት። በፊልም ካልሆነ በስተቀር ኢትዮጵያ ውስጥ በቀላሉ የምናየው ነገር አይደለም። አምፊካር መሬት ላይ መኪና ነው፤ ውሃ ላይ ጀልባ ነው። እንደ ጀልባም እንደ መኪናም የሚያገለግል የዛሬ 50 እና 60 ዓመት ኢትዮጵያ ነበራት። የዛሬ ትውልድ አያውቀውም። ይህን ታሪክ ማሳየት እንችላለን” ብለዋል። የብሔራዊ ቤተ መንግሥት ሀብቶችን ለትውልድ ለማስተማርም ለተቀረው ዓለም በማሳየትም የኢትዮጵያን ልክ ማሳየት እንደሚቻል“ይህንን በደንብ ለቱሪስቶች በማሳየት፣ በማስተማር የኢትዮጵያን ልክ ማሳየት ይቸላል። ይህን ለማድረግ እኛ አዳዲስ ታሪክ መፍጠር አይጠበቅብንም፤ ያለውን በወግ እና በልኩ ቦታው ካስቀመጥን በራሱ ከበቂ በላይ የሚያስደንቅና የሚያስደምም ብዙዎችን የሚማርክ ሆኖ እናገኘዋለን። … እዚህ ቤት ውስጥ ተራ የሚባል ዕቃ የለም። እያንዳንዱ ዕቃ ውድ ነው። ዙፋን ብንመለከት የማን ነበር ብለን ጥያቄ የምናነሳው አይደለም። ስም አለበት እንደ ማህተም። … በጣም ብዙ የሚገርሙ ብዙ ሀብቶች እዚህ ውስጥ አሉ። ብዙዎቹ በጣም በውድ የተሰሩ በወርቅ የከበሩ ናቸው። ሰው ቢያቸው ውብ የሆኑ ግን ስቶር ቢቀመጡ ትርጉም የሌላቸው” ሲሉ ነበር ያብራሩት። ቀጥለውም የብሔራዊ ቤተ መንግሥት ያዘላቸው ታሪኮች፣ ቅርሶችና የስነ ጥበብ ውጤቶች ለኢትዮጵያዊያን ኩራትም እራትም እንደሚሆኑ ጠቅሰዋል። ከኢትዮጵያ አልፎም የአፍሪካዊያን ታሪክ ማዕከል እንደሆነም እንዲሁ። “የኢትዮጵያን ታሪክ ለማሸጋገር ዕድል ይሰጣል። የትኛው የአፍሪካ ሀገር ነው በዚህ ልክ መጽሀፍ አለኝ ብሎ ማሳየት የሚችለው ብላችሁ መጠየቅ ነው። ጥንታዊ ታሪክ አለን ስንል ይህን የሚያህል መጽሀፍ ቅዱስ አለኝ የሚል የአፍሪካ ሀገር ከየትም ሊያመጣ አይችልም። ብዙ ሊነገር የሚችል ታሪክ በሚሳዝን መንገድ ታጭቆ ተቀምጧል። ሰብሰብ አድርገን ጸዳ፣ ጸዳ አድርገን ቦታው ላይ ብናስቀምጥ ልጆቻችን ታሪካቸውን፣ ማንነታቸውን ለማወቅ ዕድል ያገኛሉ። … እዚህ ቦታ ላይ ሰፊ ሰዓት ሊነገሩ የሚችሉ ታሪኮች፣ ቅርሶችና ፒክቸሮች አሉ። በዓለም ላይ ስመጥር መሪዎች ፎቶዎች ይታያሉ። ማሀተመ ጋንዲ አለ፤ ማርቲን ሉተር ኪነግ አለ። የአፍሪካ ታላላቅ መሪዎች አሉ። እያንዳንዱ የአፍሪካ ሀገር ነጻ ሲወጣ መጀመረያ መጥቶ የሚጎበኘው የአፍሪካዋን ነጻ ሀገር ኢትዮጵያ ነው። ሁሉም ሀገር ታሪኩ እዚህ አለ። የኛ ታሪክ ብቻ አይደለም። እያንዳንዱ የአፍሪካ ሀገር መሪው የመጣበት ጊዜ፤ ለምን መጣ ብለን በትክክል ቀምረን ማስቀመጥ ከቻልን እያንዳንዱ ሀገር ነጻ የወጣበትን እና ነጻ እንዲወጣ የረዳችውን ሀገር ታሪክ፣ የራሱንም ታሪክ ያይበታል። ይህ እንግዲህ ከኛም አልፎ የሌሎች የአፍሪካ ሀገሮች ታሪክም እዚህ ውስጥ እንዳለና ለእነርሱ ለማሳየትም በጣም ምቹ ይሆናል። ለእኛ ብቻ ሳይሆን እነሱም ታሪካቸውን መጥተው እንዲያዩ ማድረግ ያስችላል ማለት ነው። በአንድ ክፍል ውስጥ ይህ ሁሉ ታሪክ ታጭቋል። ሕንጻ አድሰን እያንዳንዱን ክብር ባለው ቦታ ብናስቀምጠው ታሪክ ለማወቅ ያግዛል፤ ገንዘብ እንድናገኝበትም ይረዳል፤ ቱሪስት ይስባል” በማለት ነበር ያጠቃለሉት። ብዙ ሀብትና ታሪክ በጉያው የያዘው ብሄራዊ ቤተመንግስት ለዘመናት የተደበቀው ሀብትና ታሪኩ ተገልጦ እንደ ፈረንሳዩ ቨርሳይ፤ እንደ ሩስያው ፒተርሆፍ የሚሆንበት ጊዜ ደረሰ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ከፈረንሳዩ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር ባደረጉት ንግግር መሰረት ብሔራዊ ቤተ መንግሥቱ በፈረንሳይ መንግሥት ድጋፍ ወደ ዕደሳት ገብቷል። የቨርሳይ ቤተ መንግሥት የዕድሳት ባለሙያዎች እገዛ መኖሩም ሌላ ዕድል ነው። አንድ ምዕተ ዓመት በላይ ያስቆጠረውን ይፋዊ የኢትዮ-ፈረንሳይ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትና ዘመን ተሻጋሪ ወዳጅነትም በጽኑ መሰረት ላይ ያቆመ መሆኑን ያሳዬ ነው። የአፍሪካ ቨርሳይ ያልኩት ብሔራዊ ቤተ መንግሥትም ታድሶ እንደ ፈረንሳዩ ቬርሳይ፣ እንደ ሩስያዋ ፒተርሆፍ የዕልፍ አዕላፍ ቱሪስቶች ሰርክ የሚርመሰመሱበት መዳረሻ ሊሆን እነሆ ቀኑ ደረሰ!!
ዘመን ተሻጋሪው የኢትዮጵያ እና የፈረንሳይ ወዳጅነት
Dec 21, 2024 415
ኢትዮጵያና ፈረንሳይ ረዥም ዘመን ያስቆጠረ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት ሲሆኑ ግንኙነታቸው ከ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በፊት እንደተጀመረ የታሪክ መዛግብት ያሳያሉ። የሀገራቱ ግንኙነት እየተጠናከረ ሲመጣ የወዳጅነትና የንግድ ስምምነት ወደ ማድረግ እንደተሸጋገሩና በተለይ ኢትዮጵያ የአድዋ ድልን ከተቀዳጀች በኋላ እኤአ በየካቲት ወር 1897 የኢትዮ-ጂቡቲ የድንበር ስምምነት በመፈራረም የዲፕሎማሲያዊ ትብብራቸውን መሰረት ጥለዋል። እኤአ በ1904 የኢትዮጵያና የፈረንሳይ የወዳጅነት ቢሮ በአዲስ አበባና በድሬዳዋ መከፈቱ ለግንኙነታቸው መጠናከር የበኩሉን ሚና ተጫውቷል። ግንኙነታቸው የበለጠ ተጠናክሮ እኤአ በ1907 ፈረንሳይ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት የበለጠ ለማሳደግ ኤምባሲዋን በኢትዮጵያ ከፍታለች። ከዚያ በኋላ እ.ኤ.አ በ1943 የኢትዮጵያና የፈረንሳይ የባህል ትብብር ማዕከል፣ በ1947 ሊሴ ገብረማርያም ትምህርት ቤትን፣ በ1955 የፈረንሳይ አርኪኦሎጂ ሚሽንን ወደ የፈረንሳይ ኢትዮጵያ የጥናት ማዕከል እንዲያድግ ማድረግና የሁለትዮሽ ግንኙነቱ በሁሉም መስክ እንዲጠናከር ተደርጓል። ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት በኋላም የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ጀነራል ጉሌ በኢትዮጵያ ጉብኝት ሲያደርጉ፤ በ1973 ደግሞ ሌላው የፈረንሳይ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጅ ፖምፒዱ ያደረጉት ጉብኝት ግንኙነቱ ወደ ላቀ ደረጃ መሸጋገሩን የሚያመላክት ነበር። ሁለቱ ሀገራት የዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸውን 125ኛ ዓመት ክብረ በዓል በ2014 ዓ.ም በተለያዩ መርኃ ግብሮች አክብረዋል። ከሁነቶቹ መካከል በአዲስ አበባ የሁለቱን ሀገራት የንግድ ግንኙነት ማጠናከርን አላማ በማድረግ የተካሄደው የኢንቨስትመንት ፎረም ይገኝበታል። በፎረሙ ላይ የኢትዮጵያ እና የፈረንሳይ ኩባንያዎች ተሳትፈዋል። የ125ኛ ዓመት ሁነቱ የግንኙነት ዓመታቱን ከመዘከር ባለፈ ሀገራቱ ግንኙነታቸውን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሳደግ ዳግም ቃል ኪዳናቸውን ያደሱበት ሆኗል። ግንኙነቱ መንግሥታዊ ብቻ ሳይሆን ጠንካራ የሕዝብ ለሕዝብ ትስስርንም ያካተተ ነው። የሁለቱ ሀገራት መሪዎች የጉብኝት ልውጦች የሀገራቱ ትብብር ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በጉብኝት ልውውጦች እና የሁለትዮሽ ውይይቶች ይበልጥ እየጠነከረ መጥቷል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በጥቅምት ወር 2011 ዓ.ም በአውሮፓ ሀገራት የስራ ጉብኝት ሲያደርጉ አንደኛዋ መዳረሻቸው ፈረንሳይ ነበረች። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ ከፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር ሁለቱ ሀገራት በትብብር በሚሰሩባቸው ጉዳዮች ላይ መምከራቸው ይታወቃል። ከእነዚህም መካከል በዓለም አቀፍ መድረክ አንድ በሚያደርጓቸው አጀንዳዎች፣ በጸረ ሸብርና በአየር ንብረት ለውጥ ላይ በጋራ ለመስራት መስማማታቸውም እንዲሁ። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ፈረንሳይን ከጎበኙ ከአምስት ወራት በኋላ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን በኢትዮጵያ የሁለት ቀናት ይፋዊ የስራ ጉብኝት ማድረጋቸውም የሚታወስ ነው። ማክሮን ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት ሁለቱ ሀገራት በተለያዩ መስኮች በጋራ መስራት የሚያስችላቸውን ስምምነቶች ተፈራርመዋል። ከስምምነቶቹ መካከል ፈረንሳይ ለላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ቅርስ እድሳት የሙያና የገንዘብ ድጋፍ የምታደርግበት ማዕቀፍ ይጠቀሳል። ማክሮን በወቅቱ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን መጎበኝታቸው የሚታወስ ነው። ኢንቨስትመንት እና መከላከያ ሌሎቹ ስምምነት የተፈረመባቸው መስኮች ናቸው። የሁለቱ መሪዎች የጉብኝት ልውውጦች የኢትዮጵያ እና የፈረንሳይን ትብብር በማጠናከር ረገድ ወሳኝ ሚና የተጫወተ ነው ማለት ይቻላል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከአራት ዓመታት በኋላ በየካቲት ወር 2015 ዓ.ም በፈረንሳይ የስራ ጉብኝት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር የሁለቱን ሀገራት የንግድ እና የኢንቨስትመንት ግንኙነት ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መክረዋል። በርካታ የፈረንሳይ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች በመሰማራት በሺዎች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን የሥራ እድል መፍጠራቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ። ኢትዮጵያ የግብርና ምርቶችን በተለይም ቡና ወደ ፈረንሳይ ስትልክ ፈረንሳይ በበኩሏ የትራንስፖርት ቁሳቁሶችና የህክምና መገልገያ መሳሪዎችን ወደ ኢትዮጵያ በዋናነት ትልካለች። በአሁኑ ወቅት ሁለቱ ሀገሮች በመካከላቸው ያለው የኢኮኖሚ ትስስር እየጎለበተ መጥቷል። የፈረንሳይ የአውሮፓ እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጂያን ኖኤል ባሮት በሕዳር 2017 ዓ.ም የሁለቱን ሀገራት ጠንካራ ግንኙነት ይበልጥ ማጎልበትን አላማ ያደረገ የስራ ጉብኝት በኢትዮጵያ አድርገው ነበር። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጋር የሀገራቱን የሁለትዮሽ ግንኙነት ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መምከራቸው ይታወሳል። ሚኒስትሩ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ጋርም በሁለትዮሽ፣ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ መወያየታቸውና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየምንና በፈረንሳይ መንግሥት የተመሠረተውን የሊሴ ገብረ ማርያም ትምህርት ቤት መጎብኘታቸውም እንዲሁ። ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በ1960ዎቹ ከመልካ ቁንጥሬ መካነ ቅርስ ለምርምር ወደ ፈረንሳይ ተወስደው የነበሩ ጥንታዊ የሰው ዘር የተገለገለባቸውን የድንጋይ መሣሪያዎች ለቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ ማስረከባቸው ይታወሳል። በወቅቱ በፈረንሳይ መንግሥት በኢትዮጵያ የሚተገበር ቀጣይነት ያለው የኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ፕሮጀክት ይፋ የተደረገ ሲሆን ፕሮጀክቱ በ2011 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እና የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን የላሊበላ ውቅር አብያተ-ክርስቲያናትና የብሔራዊ ሙዚየም እድሳትን አስመልክቶ ስምምነት የደረሱበት ስራ አካል ነው። በሚኒስትሩ ጉብኝት ወቅት የትምህርት ሚኒስቴር ከፈረንሳይ ጋር በዘርፉ ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር የሚያስችለውን ስምምነት ተፈራርሟል። ስምምነቱ ፈረንሳይ ለኢትዮጵያ የተለያዩ ነጻ የትምህርት እድሎችን ለመስጠት፣ እንዲሁም በሊሴ ገብረማሪያም ትምህርት ቤት የስኮላር ሺፕ መርሃ ግብሮችን ለማጠናከር የሚያስችል ነው። ባሮት የአፍሪካ ሕብረት ዋና መቀመጫ በሆነችው አዲስ አበባ በተካሄደው የአፍሪካ ሕብረት እና ፈረንሳይ የከፍተኛ ደረጃ ስትራቴጂካዊ ምክክር መድረክ ላይም ተሳትፎ አድርገዋል። አቪዬሽን ሌላኛው የአገራቱ የወዳጅነት ማጋመጃ ዘርፍ ኢትዮጵያ እና ፈረንሳይ በአቪዬሽን ዘርፍ ያላቸው ትብብርም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል። ሁለቱ አገራት በ2009 ዓ.ም በሲቪል አቪዬሽን፣ በአየር ትራንስፖርት እና መሰረተ ልማት ዘርፎች ትብብራቸውን ለማጠናከር የሚያስችል ስምምነት ተፈራርመዋል። በ2008 ዓ.ም ተመሳሳይ ስምምነት አካሂደው የነበረ ሲሆን የ2009 ዓ.ም ያደረጉት ስምምነት ከወቅቱ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ፍላጎት ጋር እንዲጣጣም በማድረግ በድጋሚ ተሻሽሎ እንደተፈረመ በወቅቱ ተገልጿል። ስምምነቱ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ የሚያደርገውን ሳምንታዊ በረራ የሚያሳድግ እና በቀጣይም ተጨማሪ በረራዎችን ለማድረግ የሚያስችል ነው። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ የመጀመሪያ የሆነውን ኤር ባስ ኤ350-1000 "Ethiopia land of origins" የተሰኘ የመንገደኞች አውሮፕላን ከፈረንሳዩ የኤር ባስ ኩባንያ በጥቅምት ወር 2017 ዓ.ም መረከቡ ይታወቃል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዚህ ቀደም የኤ350-900 አውሮፕላኖችን ጨምሮ ሌሎች በአፍሪካ የመጀመሪያ የሆኑ አውሮፕላኖችን ቀድሞ በማስገባት የሚታወቅ ነው። ኢትዮጵያ ኤ350-1000 የኤር ባስ አውሮፕላን የተረከበች የመጀመሪያዋ አፍሪካዊት አገር መሆኗ ካለው ታሪካዊ ስኬት ጎን ለጎን ሁለቱ አገራት በአቪዬሽን ዘርፍ ያላቸው ትብብር እያደረገ መምጣቱን የሚያመላክትም ነው። በአገራቱ መካከል ያለውን ጠንካራ ግንኙነት ወደ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ከፍ የማድረግ መሻት አለ። ኢትዮጵያ የፈረንሳይ ኩባንያዎች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች እያደረጉ ያሉትን ተሳትፎ በማጠናከር የሁለቱ አገራት የንግድ እና ኢንቨስትመንት ትብብር እንዲያድግ ፍላጎት አላት። ሁለቱ አገራት የጋራ ፍላጎታቸው በሆኑ የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን የትብብር ጉዳዮች ላይ ያላቸው ትስስር እንዲያድግም ትሻለች። ፈረንሳይም የኢትዮጵያን አገራዊ ምክክር ሂደት እና የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ትግበራን ጨምሮ በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን ለማምጣት እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኗን ገልጻለች። ኢትዮጵያ እያከናወነች ላለችው ፈጣን የልማት እንቅስዋሴ ፈረንሳይ የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ እንደምትቀጥልም እንዲሁ። የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ይፋዊ የስራ ጉብኝትም ይሄንኑ ከፍታ የሚያሳይ ይሆናል። ጉብኝቱ የአገራቱን ጠንካራ ወዳጅነት ይበልጥ የማጽናት ፍላጎት አካል ነው ተብሎ ሊወሰድም ይችላል።
ከሀገራዊ ለውጡ በኋላ ይበልጥ የተጠናከረው የኢትዮጵያና ፈረንሳይ ወዳጅነት
Dec 21, 2024 333
የኢትዮጵያና ፈረንሳይ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ዘመናትን የተሻገረ ቢሆም በተለይ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ወደ ስልጣን መምጣትን ተከትሎ በብዙ ዘርፎች ግንኙነቱ ይበልጥ ጎልብቷል። በዚህም በሀገራቱ መካከል በንግድና ኢንቨስትመንት፣ በትምህርት፣ በሰላምና ጸጥታ፣ በአቪዬሽንና በሌሎችም መስኮች የጠበቀ ትስስር መፍጠር ተችሏል። የሀገራቱ ትብብር ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በመሪዎች የጉብኝት ልውውጦች እና የሁለትዮሽ ውይይቶች ይበልጥ እየጠነከረ መጥቷል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በጥቅምት ወር 2011 ዓ.ም በአውሮፓ ሀገራት የስራ ጉብኝት ባደረጉበት ወቅት አንደኛዋ መዳረሻቸው ፈረንሳይ ነበረች። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በወቅቱ ከፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር ሁለቱ ሀገራት በትብብር በሚሰሩባቸው ጉዳዮች ላይ መምከራቸው ይታወቃል። ከእነዚህ መካከልም በዓለም አቀፍ መድረክ አንድ በሚያደርጓቸው አጀንዳዎች፣ በጸረ ሽብርና በአየር ንብረት ለውጥ ላይ በጋራ ለመስራት ተስማምተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ፈረንሳይን ከጎበኙ ከአምስት ወራት በኋላ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን በኢትዮጵያ የሁለት ቀናት ይፋዊ የስራ ጉብኝት አድርገዋል። ፕሬዚደንት ማክሮን ኢትዮጵያን በጎበኙበት ወቅት ሁለቱ ሀገራት በተለያዩ መስኮች መስራት የሚያስችላቸውን ስምምነቶች ተፈራርመዋል። ከስምምነቶቹ መካከል ፈረንሳይ ለላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ቅርስ እድሳት የሙያና የገንዘብ ድጋፍ የምታደርግበት ማዕቀፍ ይጠቀሳል። ፕሬዚደንት ማክሮን በወቅቱ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን መጎበኝታቸው የሚታወስ ነው። ኢንቨስትመንት እና መከላከያ ሌሎቹ ስምምነት የተፈረመባቸው መስኮች ናቸው። የሁለቱ መሪዎች የጉብኝት ልውውጦች የኢትዮጵያ እና የፈረንሳይን ትብብር በማጠናከር ረገድ ወሳኝ ሚና ተጫውቷል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ከአራት ዓመታት በኋላ በየካቲት ወር 2015 ዓ.ም በፈረንሳይ የስራ ጉብኝት አድርገዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን ጋር የሁለቱን ሀገራት የንግድ እና ኢንቨስትመንት ግንኙነት ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መምከራቸው ይታወሳል። በርካታ የፈረንሳይ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች በመሰማራት በሺዎች ለሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን የሥራ እድል መፍጠራቸውን መረጃዎች ያመለክታሉ። ኢትዮጵያ የግብርና ምርቶችን በተለይም ቡና ወደ ፈረንሳይ ስትልክ ፈረንሳይ የትራንስፖርት ቁሳቁሶችና የህክምና መገልገያ መሳሪዎችን ወደ ኢትዮጵያ በዋናነት ትልካለች። በአሁኑ ወቅት ሁለቱ ሀገሮች በመካከላቸው ያለው የኢኮኖሚ ትስስር እየጎለበተ መጥቷል። የፈረንሳይ የአውሮፓ እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጂያን ኖኤል ባሮት በሕዳር 2017 ዓ.ም በኢትዮጵያ ያደረጉት ጉብኝት የሁለቱን ሀገራት ጠንካራ ግንኙነት ይበልጥ ማጎልበትን አላማ ያደረገ ነበር። የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ጋር የሀገራቱን የሁለትዮሽ ግንኙነት ማጠናከር በሚቻልበት ሁኔታ ላይ መክረዋል። ባሮት ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ጋርም በሁለትዮሽ፣ ቀጣናዊ እና ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ላይ መወያየታቸው ይታወሳል። ሚኒስትር ጂያን ኖኤል ባሮት በቆይታቸው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየምንና በፈረንሳይ መንግሥት የተመሠረተውን የሊሴ ገብረ ማርያም ትምህርት ቤት ጎብኝተዋል። ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በ1960ዎቹ ከመልካ ቁንጥሬ መካነ ቅርስ ለምርምር ወደ ፈረንሳይ ተወስደው የነበሩ ጥንታዊ የሰው ዘር የተገለገለባቸውን የድንጋይ መሣሪያዎች ለቱሪዝም ሚኒስትር ሰላማዊት ካሳ ማስረከባቸውም እንዲሁ። በወቅቱ በፈረንሳይ መንግሥት በኢትዮጵያ የሚተገበር ቀጣይነት ያለው የኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ፕሮጀክት ይፋ ተደርጓል። ፕሮጀክቱ በ2011 ዓ.ም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) እና የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን የላሊበላ ውቅር አብያተ-ክርስቲያናትና የብሔራዊ ሙዚየም እድሳትን አስመልክቶ ስምምነት የደረሱበት ስራ አካል ነው። በሚኒስትሩ ጉብኝት ወቅት የትምህርት ሚኒስቴር ከፈረንሳይ ጋር በዘርፉ ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር የሚያስችለውን ስምምነት ተፈራርሟል። ስምምነቱ ፈረንሳይ ለኢትዮጵያ የተለያዩ ነጻ የትምህርት እድሎችን ለመስጠት፣ እንዲሁም በሊሴ ገብረማሪያም ትምህርት ቤት የስኮላር ሺፕ መርሃ ግብሮችን ለማጠናከር የሚያስችል ነው። ባሮት የአፍሪካ ሕብረት ዋና መቀመጫ በሆነችው አዲስ አበባ በተካሄደው የአፍሪካ ሕብረት እና ፈረንሳይ የከፍተኛ ደረጃ ስትራቴጂካዊ ምክክር መድረክ ላይም ተሳትፎ አድርገዋል። ኢትዮጵያ የፈረንሳይ ኩባንያዎች በተለያዩ የኢንቨስትመንት መስኮች እያደረጉ ያሉትን ተሳትፎ በማጠናከር የሁለቱ ሀገራት የንግድ እና ኢንቨስትመንት ትብብር እንዲያድግ ፍላጎት አላት። ሁለቱ ሀገራት የጋራ ፍላጎታቸው በሆኑ የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን የትብብር ጉዳዮች ላይ ያላቸው ትስስር እንዲያድግም ትሻለች። ፈረንሳይም የኢትዮጵያን ሀገራዊ ምክክር ሂደት እና የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ትግበራን ጨምሮ በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን ለማምጣት እየተደረጉ ያሉ ጥረቶችን ለመደገፍ ዝግጁ መሆኗን ገልጻለች። ኢትዮጵያ እያከናወነች ላለችው ፈጣን የልማት እንቅስቃሴ ፈረንሳይ የምታደርገውን ድጋፍ አጠናክራ እንደምትቀጥልም እንዲሁ። የፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኢማኑኤል ማክሮን በድጋሚ ለይፋዊ የስራ ጉብኝት ወደ ኢትዮጵያ መምጣትም ይሄንኑ ከፍታ የሚያሳይ ነው። ጉብኝቱ የሀገራቱን ጠንካራ ወዳጅነት ይበልጥ የማጽናት ፍላጎት አካል ነው ተብሎ ሊወሰድም ይችላል።
አቪዬሽን የኢትዮጵያና ፈረንሳይ ወዳጅነት ማሳያ
Dec 21, 2024 238
በመቶ ዓመታት የሚቆጠረው የኢትዮጵያና ፈረንሳይ ግንኙነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተጠናከረ እኤአ በ1907 ፈረንሳይ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት የበለጠ ለማሳደግ ፈረንሳይ ኤምባሲዋን በኢትዮጵያ እንድትከፍት አስችሏል። ከዚህ በኋላም በብዙ መስኮች ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነታቸው እያደገና እየጎለበተ መጥቶ በንግድና ኢንቨስትመንት፣ በትምህርት፣ በሰላምና ጸጥታ የጠበቀ ትስስር መፍጠር አስችሏቸዋል። ኢትዮጵያ እና ፈረንሳይ በአቪዬሽን ዘርፍም ያላቸው ትብብር ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መጥቷል። ሁለቱ ሀገራት በ2009 ዓ.ም በሲቪል አቪዬሽን፣ በአየር ትራንስፖርት እና መሰረተ ልማት ዘርፎች ትብብራቸውን ማጠናከር የሚያስችል ስምምነት ተፈራርመዋል። በ2008 ዓ.ም ተመሳሳይ ስምምነት አካሂደው የነበረ ሲሆን 2009 ዓ.ም ያደረጉት ስምምነት ከወቅቱ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ፍላጎት ጋር እንዲጣጣም በማድረግ በድጋሚ ተሻሽሎ እንደተፈረመ በወቅቱ ተገልጿል። ስምምነቱ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ ፈረንሳይ የሚያደርገውን ሳምንታዊ በረራ የሚያሳድግ እና በቀጣይም ተጨማሪ በረራዎችን ለማድረግ የሚያስችል ነው። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ የመጀመሪያ የሆነውን ኤር ባስ ኤ350-1000 "Ethiopia land of origins" የተሰኘ የመንገደኞች አውሮፕላን ከፈረንሳዩ የኤር ባስ ኩባንያ በጥቅምት ወር 2017 ዓ.ም መረከቡ ይታወቃል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዚህ ቀደም የኤ350-900 አውሮፕላኖችን ጨምሮ ሌሎች በአፍሪካ የመጀመሪያ የሆኑ አውሮፕላኖችን ቀድሞ በማስገባት የሚታወቅ ነው። ኢትዮጵያ ኤ350-1000 የኤር ባስ አውሮፕላን የተረከበች የመጀመሪያዋ አፍሪካዊት ሀገር መሆኗ ካለው ታሪካዊ ስኬት ጎን ለጎን ሁለቱ ሀገራት በአቪዬሽን ዘርፍ ያላቸው ትብብር እያደረገ መምጣቱን የሚያመላክትም ነው።
በአፍሪካ ሠማያት ሥር የነገሰዉ አየር መንገድ
Dec 17, 2024 432
ዩሱፍ ባንጉራ ይባላሉ፡፡ እንግሊዝ ለንደን ከሚገኘዉ ኢኮኖሚክስ እና የፖለቲካ ሳይንስ ኮሌጅ የዶክተሬት ድግሪያቸውን አግኝተዋል፡፡ ለ22 ዓመታት በተለያዩ የምርምር ፕሮጀክቶች ላይ ሰርተዋል፡፡ በናይጄሪያ በአህመዱ ቤሎ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስን ለስምንት ዓመታት አስተምረዋል፡፡ ተቀማጭነቱን ናይጀሪያ ባደረገው ‘ኢንተርቬንሽን’(Intervention) ለሚሰኝ የበይነ መረብ ጋዜጣ ፅሁፎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡ ከሰሞኑ ስለኢትዮጵያ አየር መንገድ ስኬት ያቀረቡትን ፅሁፍ ወደ አማርኛ መልሰነዋል፡፡ እነሆ! “የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከኢትዮጵያ አልፎ ዓለም አቀፍዊነትን ተላብሷል። ዛሬ ላይ ኢትዮጵያ በአቬሽን ዘርፍ ከአፍሪካ ሠማያት ባለፈ የዓለም ልዕለ ኃያል አገር ሆናለች ”ይላሉ ዩሱፍ ባንጉራ (ዶ/ር) ዩሱፍ ባንጉራ (ዶ/ር) በአፍሪካ ሠማያት ሥር የነገሰዉ አየር መንገድ የአፍሪካ አቪዬሽን ኢንዱስትሪ ፋና ወጊ ነው፤ የአፍሪካ ሠማያት ልዕለ ኅይል። በየዓመቱ ሚሊዮኖችን ያጓጉዛል፤ በመላ ዓለም የመዳረሻዎቹ ብዛት የትየለሌ ነው። በሚያመነጨው ገቢ በአፍሪካ ግንባር ቀደም ነው። ይህ በአፍሪካ ሠማያት ላይ የነገሰው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ነው። እ.ኤ.አ በ2023 ብቻ 13 ነጥብ 8 ሚሊየን መንገደኞችን አጓጉዟል። በ40 አፍሪካ ሀገራት ዉስጥ 60 መዳረሻዎች አሉት። በዓለም ዙሪያ ወደ 136 ከተሞች ይበራል። እ.ኤ.አ 2023/24 ብቻ አየር መንገዱ 7 ነጥብ 2 ቢሊየን ዶላር ገቢ አግኝቷል። በዓለም አቀፍ ደረጃ በመዳረሻ ብዛት አራተኛዉ ግዙፍ አየር መንገድ ነው። ከአፍሪካ ግዙፍ አየር መንገዶች ግንባር ቀደሙ ነው። በ2023 ብቻ አየር መንገዱ የ154 አዉሮፕላኖች ባለቤት ነበር። የግብፅ አየር መንገድ 70 አዉሮፕላኖች አሉት። በአዉሮፕላን ብዛት ሁለተኛ ደረጃ ላይ ይቀመጣል። የሞሮኮዉ አየር መንገድ ኤር ማሮክ በ51 አዉሮፕላኖች ሦስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል። የኬኒያ አየር መንገድ 34 እንዲሁም የደቡብ አፍሪካ አየር መንገድ 17 አውሮፕላኖችን ይዘው ይከተላሉ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በመዳረሻ ብዛትም ቀዳሚ ነዉ፡፡ የሞሮኮዉ ኤር ማሮክ በ24 የአፍሪካ ከተሞች መዳረሻ አለዉ። የግብፅ አየር መንገድ ወደ 44 የአፍሪካ ከተሞች የሚበር ቢሆንም 16ቱ በዚያዉ በግብፅ ዉስጥ የሚገኙ ናቸዉ። በአፍሪካ ዉስጥ በመዳረሻ ብዛት ሊወዳደረዉ የሚችለዉ የኬኒያ አየር መንገድ ብቻ ነው። የኬኒያ አየር መንገድ በአፍሪካ ወደ 56 ከተሞች የበረራ መዳረሻዎች አሉት። ሆኖም የኢትዮጵያ አየር መንገድ ወደ 60 የአፍሪካ ከተሞች በመብረር ብልጫዉን ይይዛል። የዓለም አቀፍ መደረሻቸዉን ስናይ ልዩነታቸዉ ሰፊ ነዉ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከአፍሪካ ዉጭ በሚገኙ 96 ከተሞች ሲበር፥ የኬኒያ ኤር ዌይስ ግን ወደ 14 ከተሞች ብቻ ይደርሳል። በሌላ አገላለፅ አንድ ሰዉ ከአፍሪካ ወደ እስያ፣ አውሮፓ፣ ሰሜን አሜሪካ ወይም ላቲን አሜሪካ የሚሄድ ከሆነ ከኬኒያ አየር መንገድ ይልቅ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ምርጫዉ ያደረጋል ማለት ነዉ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ የመጀመሪያው ዓለም አቀፍ አየር መንገድ ነው። የአየር መንገዱ በቻይና 10 ከተሞች፣ በአሜሪካ 8 ከተሞች፣ በህንድ 6 ከተሞች የበረራ መደረሻ አሉት። ወደ አብዛኛዎቹ የምዕራብ አውሮፓ አገሮች፤ ሩሲያ እና ፖላንድ ውስጥ ያሉ ከተሞች ጨምሮ ይበራል። በአብዛኛዎቹ የመካከለኛው ምሥራቅ እና የእስያ አገሮች በሚገኙ ከተሞች; እንዲሁም በላቲን አሜሪካ ውስጥ ብራዚል፣ አርጀንቲና፣ ቺሊ እና ኮሎምቢያ መዳረሻዎች አሉት። በአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ታሪክ ውስጥ በዋናነት የሚነሳው የኢትዮጵያ አየር መንገድ አፍሪካ እርስ በእርስ እና ከተቀረው ዓለም ጋር በማስተሳሰር ጉልህ ሚና እየተጫወተ ነው። እንደ ናይጄሪያ ኤርዌይስ፣ ጋና ኤርዌይስ እና ኤር አፍሪክ ያሉ ነባር አየር መንገዶች አገልግሎታቸዉ በአካባቢያዊ ደረጃ የተወሰነ ነዉ። የኢትዮጵያን አየር መንገድ ለአፍሪካዊያን ጥራት ያለው አገልግሎት በመስጠት የአህጉሪቷ ኩራት መሆኑን አስመስክሯል። በአፍሪካዊያን ትስስር ውስጥ ትልቅ ሚና እየተጫወተ ያለ አየር መንገድ ነዉ። አፍሪካዊያንን እርስ በርስ እና ከሌላዉ ዓለም ጋር በተመጣጣኝ ዋጋ ያገናኛል። አየር መንገዱ ባለፉት አምስት ዓመታት የአፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ ሽልማትን በተከታታይ ማሸነፍ ችሏል። አሁን ላይ ብዙ የአፍሪካ ሀገራት አየር መንገዶቻቸውን ለማስፋፋት ወይም ከኪሳራ ለመታደግ ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር መስራት ይፈልጋሉ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ከዛምቢያ ኤርዌይስ፣ ማላዊ ኤርላየን፣ ኤር ኮንጎ እና ጊኒ ኤርዌይስ 50 በመቶ የሚጠጋ ድርሻ አለዉ። በ2023 በምዕራብ አፍሪካ ምርጥ አየር መንገድ ተብሎ ከተሸለመዉ አስካይ አየር መንገድ ደግሞ 27 በመቶ ድርሻ አለው። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአስካይ አየር መንገድ ስትራቴጂክ እና ቴክኒካል ኦፕሬሽን ይመራል። ኢትዮጵያዊ ዋና ሥራ አስፈፃሚ ተመድቦለታል። በአየር መንገዱ በነበረን ቆይታ ያየነዉ.... ይህን የአፍሪካ ኩራት የሆነዉን አየር መንገድ በቅርቡ ወደ ደቡብ አፍሪካ፣ ኢትዮጵያ እና ናይጄሪያ ባደረግነው ጉዞ በቅርበት አይተነዋል። አየር መንገዱን በስድስት ሳምንታት ጊዜ ውስጥ ስምንት ጊዜ ተጠቀመናል። ከጄኔቫ-አዲስ አበባ፣ ከአዲስ አበባ-ዊንድሆክ፣ ከኬፕታውን-አዲስ አበባ፣ ከአዲስ አበባ-ጄኔቫ፣ ከጄኔቫ-አዲስ አበባ፣ ከአዲስ አበባ-አቡጃ፣ ከሌጎስ-አዲስ አበባ እና ከአዲስ አበባ-ጄኔቫ ተንሸራሽረንበታል። በአውሮፓ የሚኖሩ ብዙ ናይጄሪያውያን በቀጥታ ወደ ሌጎስና አቡጃ በቀጥታ ከመብረር ይልቅ የኢትዮጵያን አየር መንገድ በመጠቀም በአዲስ አበባ አድርጎ መጓዝ ወጭ ቆጣቢ እንደሆነ ይናገራሉ። ከሁለት ሳምንት በፊት ወደ አቡጃ እና ሌጎስ ስንጓዝ የኢትዮጵያ አየር መንገድን በመምረጣችን የትኬታችንን ዋጋ ከ50 ከመቶ በላይ ቀንሰናል። ብዙ ተሳፋሪዎች አሁን ተመሳሳይ ስሌት አላቸዉ። ከአዲስ አበባ ወደ ጄኔቫ የሄድንበት በረራ ከሌጎስ ወደ ማንቸስተር የሚሄዱ መንገደኞች ጋር ነበር። አዲስ አበባ ቦሌ አየር ማረፊያ ወደ አውሮፓ፣ እስያ እና መካከለኛው ምሥራቅ ትራንዚት በሚያደርጉ የምዕራብ፣ ምሥራቅ እና ደቡብ አፍሪካዊያን የተሞላ ነበር። ወደተለያዩ አገራት ለሚገዙ አፍሪካዊያን አዲስ አበባ የቦሌ ኤርፖርት ዋና የአፍሪካዊያን መዉጫና መግቢያ በር ሆኖ ያገለግላል። አዲስ አበባ ቦሌ ኤርፖርት አራት ጊዜ ትራንዚት ባደረግንበት ወቅት ልክ ትልቅ ዓለም አቀፍ የንግድ ከተማ ውስጥ እንደሆንን እየተሰማን ነበር። አየር መንገዱ ለደህንነት ቅድሚያ ይሰጣል። ከተለያዩ አህጉራት የመጡ ብዙ ቁጥር ያላቸው ትራንዚት መንገደኞች ጥብቅ የደህንነት ፍተሻዎች ይደረግላቸዋል። ጄምስ ፒርሰን፣ በአየር መንገዱ ቡኪንግ መረጃ መሠረት በ2023፤ 11 ሚሊዮን መንገደኞች በአዲስ አበባ ቦሌ አየር ማረፊያ በኩል ትራንዚት ማድረጋቸዉን ይናገራል። በአዲስ አበባ ቦሌ ኤርፖርት ዉስጥ ከአስሩ መንገደኞች ሰባቱ ትራንዚተር ናቸዉ። ለዚህ ከፍተኛ ቁጥር የትራንዚተር ቁጥር ቀጣናዊ እና ክፍለ አህጉራዊ የገበያ ቦታዎች አስተዋፅኦ አበርክተዋል። ወደ አፍሪካ ለሚደረጉ በረራዎች ዱባይን ተክቷል…. አዲስ አበባ የአፍሪካ ዱባይ ሆናለች፡፡ መግቢያቸዉም መዉጫቸዉም አዲስ አበባ ናት፡፡ የኢትዮጵያ መንግሥት አየር መንገዱ የአፍሪካዊያን የመግቢያ እና መዉጫ በር መሆኑን ተረድተዋል። ለተሳፋሪዎች በርካታ የደህንነት ፍተሻዎች ይደረጋል። ትራንዚተሮች ሁለት ጠንካራ ፍተሻ እና አንድ ቀላል ፍተሻዎችን ማለፍ ይኖርባቸዋል። ጉዟቸው ከቦሌ ኤርፖርት የሚጀምሩ መንገደኞች አጠቃላይ አራት ፍተሻዎችን ማለፍ ይኖርባቸዋል። እነዚህ በርካታ ፍተሻዎች አሰልቺ እና አድካሚ ሊመስሉ ይችላሉ። ነገር ግን ለመንገደኞቹ ደህንነት ከፍተኛ ጥንቃቄ ለሚያደርግ አየር መንገድ የግድ ነዉ። መንግሥታት ትርፋማ ድርጅቶችን ማስተዳደር ይችላሉ? እንደ ኒዮሊበራል የገበያ አስተሳሰብ መንግሥት ትርፋማ የንግድ ድርጅቶችን በባለቤትነት ሲያስተዳድር ብልሹ አሰራር ይስፋፋል ብሎም ድርጅቱን ለኪሳራ ይዳርገዋል። መከራከሪያቸዉ ደግሞ መንግሥት ትላልቅ የንግድ ተቋማትን ሲያስተዳድር ለኃላፊዎቹ ፖለቲካዊ ሹመት ይሰጣል። በመሆኑም እነዚህን ተሿሚዎች ቢያጠፉ ለመቅጣት ወይም ከሥራ ለማባረር ይቸግራል በማለት መንግሥት አትራፊ የንግድ ተቋማትን ማስተዳደ እንደሌለበት ይገልጻል። ይህ ካልሆነ ድርጅቱ ይከስራል ወይም ከገበያ ይወጣል። ነገር ግን ይህ የኒዮሊበራል የገበያ ፍልስፍና በኢትዮጵያ አየር መንገድ አይሰራም። አየር መንገዱ ሙሉ በሙሉ በመንግሥት ሥር ይተዳደራል። እዚህ ላይ ጥያቄ መሆን የሚገባዉ በአፍሪካ በመንግሥት ባለቤትነት የተያዙ አየር መንገዶች ለምን ለኪሳራ ተዳረጉ የሚለዉ ነዉ። ለምሳሌ የደቡብ አፍሪካ አየር መንገድ በመንግሥት ቢተዳደርም በገበያዉ ለመቆየት እየተንገዳገደ ይገኛል። የኢትየጵያ አየር መንገድ በ1946 እና 1975 መካከል ባሉት ጊዜያት ከትራንስ ወርልድ አየር መንገድ /TWA/ ጋር በነበረው ስትራቴጂካዊ አጋርነት የቴክኖሎጂ አጠቃቀም አቅምን አሳድጓል። እንዲሁም መልካም የሥራ ባህል እንዲያዳብር እንደረዳዉ አቶ አርከበ ዕቑባይ እና ታፈረ ተስፋቸዉ ያቀረቡት ጽሑፍ ያሳያል። ከአጼ ኃይለ ሥላሴ ከመንበረ ሥልጣን መወገድ በኋላ ወታደራዊ ሶሻሊስት መንግሥት ሥልጣኑን ሲቆናጠጥ አየር መንገዱ ከሞላ ጎደል ለኪሣራ ተዳርጎ ነበር። ከ1991 ወዲህ ያሉ መንግሥታት የኢትዮጵያ አየር መንገድን ተቋማዊ ነፃነት እንዲኖረዉ አድርገዋል። አየር መንገዱ ዓለም አቀፍ የንግድ መርሆች መሠረት በማድረግ ሥራውን ያከናዉናል። ይህ ነፃነቱ በአፍሪካ የአቪዬሽን መሪ ሆኖ በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ጎልቶ እንዲወጣ አስችሎታል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ መንግሥታት ዓለምአቀፍ ትርፋማ ተቋማትን መፍጠርና ማስተዳደር እንደሚችሉ ማሳያ ይሆናል። የዚህ ፅሁፍ ሀሳብ የደራሲዉ መሆኑን እንገልፃለን፡፡
ከካፋ እና ሸካ ጥቅጥቅ ደኖች እስከ ጨበራ ጩርጩራ ብሄራዊ ፓርክ
Dec 16, 2024 668
ኢትዮጵያ ለምለም ምድር መሆኗን ሁነኛ ማሳያ ከሆኑት መካከል የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል አንዱ ነው፡፡ ክልሉ በሁሉም አቅጣጫዎች ውብ የተፈጥሮ ፀጋን የተላበሰ ስለመሆኑ በሚያሳዩ አረንጓዴ እጽዋት የተሞላ ነው፡፡ በክልሉ የሚገኙት ካፋ፣ ሸካ፣ ቤንች ሸኮ፣ ዳውሮ፣ ምዕራብ ኦሞ እና ኮንታ ዞኖች አረንጓዴ የለበሱ ድንቅ የተፈጥሮ ጸጋ መገኛዎች ናቸው፡፡ ይህም ክልሉን ትልቅ የቱሪዝም መዳረሻ አድርጎታል፡፡ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ከፍተኛ የቱሪዝም መዳረሻ ስፍራ እንዲሆን ያስቻለው አረንጓዴነቱ(በእጽዋት መሸፈኑ) መሆኑ ይጠቀሳል፡፡ አረንጓዴ ያስባለው ደግሞ ዓይንን የሚማርኩ እና መንፈስን የሚያድሱ ጥቅጥቅ ያሉ ደኖች በብዛት መኖራቸው ነው፡፡ ለዚህም አብነት ሆኖ የሚነሳው በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሳይንስ፣ የትምህርትና ባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) የተመዘገበው የሸካ ጥብቅና ጥቅጥቅ ደን ነው፡፡ ደኑ(Biosphere) በውስጡ ጫካ፣ የቀርከሃ ዛፎች፣ በውሃ ዙሪያ የሚገኝ ርጥብ መሬት፣ የእርሻ መሬት፣ እንዲሁም የገጠር እና የከተማ ሰፈራ አካባቢዎችን የያዘ ነው፡፡ ከቀዝቃዛ ጀምሮ እጅግ እርጥበታማ የደጋ ስፍራዎች እስከ ሞቃታማ ቆላ ድረስ የአየር ጠባይ የሚስተናገድበትም ነው፡፡ የዩኔስኮ መረጃ እንደሚያመለክተው፣ የሸካ ጥብቅ እና ጥቅጥቅ ደን አጠቃላይ 238ሺህ 750 ሄክታር መሬት ይሸፍናል። የበርካታ እንስሳት እና እጽዋት ዝርያዎች መኖሪያም ነው፡፡ ከ300 በላይ ትላልቅ እጽዋቶች፣ 50 አጥቢ እንስሳት፣ 200 አዕዋፋት እና 20 የእንቁራሪት አስተኔ ዝርያዎች መገኛም ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ብርቅዬና ሀገር በቀል የሆኑ 55 የእጽዋት፣ 10 አዕዋፋት እና 38 የመጥፋት አደጋ የተጋረጠባቸው እንስሳትና እጽዋት ዝርያዎች እንደሚገኙም ዩኔስኮ በድረገጹ አስፍሯል፡፡ አረቢካ ቡና፣ ቁጥቋጦ እና ሌሎች የእጽዋት ዝርያዎችም በደኑ ውስጥ ይገኛሉ፡፡ በእንስሳት በኩል በውሃ ውስጥም በየብስም የሚኖሩ፣ ትላልቅና ትናንሽ አጥቢዎች፣ ተሳቢዎች እና የአዕዋፋት ዝርያዎች መኖሪያቸውን በደኑ ውሰጥ አድርገዋል፡፡ ጃርት፣ የተለያዩ የዝንጀሮ ዝርያዎች፣ የአፍሪካ ጎሽ፣ አንበሳ፣ ነብር፣ የአፍሪካ ጥርኝ፣ የኢትዮጵያ ጥንቸል፣ የአቢሲኒያ ባለጥቁርና ቢጫ ቀለም ወፍ እና ግንደ-ቆርቁር ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ዩኔስኮ የሸካ ጥብቅና ጥቅጥቅ ደንን የመዘገበው በአውሮፓውያኑ 2012 ነው፡፡ ከሸካ በተጓዳኝ የካፋ ጥብቅና ጥቅጥቅ ደን(Biosphere) በዩኔስኮ የተመዘገበ ሌላኛው በክልሉ የሚገኝ የቱሪዝም መዳረሻ ነው፡፡ በካፋ ዞን የሚገኘው ደኑ፣ በዓለማችን ተወዳጅ የሆነውውን የአረቢካ ቡና መገናኝ ቦታን ያካልላል፡፡ የብዝሃ- ሕይወት መገኛ የሆነው ደኑ፣ ዩኔስኮ እንደመዘገበው 760 ሺህ 144 ሄክታር መሬት ይሸፍናል። 5 ሺህ የተለያዩ ዓይነት እጽዋቶች መገኛም ነው፡፡ ከእነዚህም ውስጥ የተለያዩ ዛፎች፣ ቁጥቋጦዎች እና የጫካ ቡና በስፋት ይገኝበታል፡፡ ከእጽዋት ዝርያዎች መካከል 110 የሚሆኑት ሀገር በቀል ናቸው፡፡ አረቢካ ቡና፣ ኮረሪማ፣ የቀርከሃ ዛፎች እና ሌሎችም የእጽዋት ዝርያዎች በስፋት በደኑ ይገኛሉ፡፡ በተጨማሪም 300 የሚጠጉ የአጥቢ እንስሳት ዝርያዎች እንዳሉ ይነገራል፡፡ የለሊት ወፍ፣ አይጠ-ሞጎጥ፣ የተለያዩ የዝንጀሮ ዝርያዎች፣ ጉማሬ፣ ጎሽ፣ አጋዘን፣ ጃርት፣ ከርከሮ፣ ጅብ፣ የጫካ አሳማ፣ አንበሳ፣ ነብር፣ ፍልፈል፣ ጥርኝ፣ ቀበሮ እና ጉሬዛ ከእንስሳቱ መካከል ይገኙበታል፡፡ የካፋ ጥብቅ እና ጥቅጥቅ ደን በፈረንጆቹ ሰኔ ወር 2010 ነበር በዩኔስኮ የተመዘገበው፡፡ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል ከታደላቸው ሌሎች የተፈጥሮ ሃብቶች መካከል የጨበራ ጩርጩራ ብሄራዊ ፓርክ አንዱ ነው፡፡ ፓርኩ በዳውሮ እና ኮንታ ዞኖች መካከል የሚገኝ ነው፡፡ በአጠቃላይ 1ሺህ 410 ስኩዌር ኪሎ ሜትር የቆዳ ስፋት ይሸፍናል፡፡ ከ1ሺህ 200 እስከ 2ሺህ 300 ሚሊ ሜትር ዓመታዊ የዝናብ መጠን ይመዘገብበታል፡፡ ሙቀት ደግሞ ከ10 ድግሪ ሴልሺየስ እስከ 29 ድግሪ ሴልሺየስ። ከመጋቢት እስከ መስከረም ወራት ድረስ እርጥበታማ ወቅቶች ሲሆኑ፣ ከታህሳስ እስከ የካቲት ደግሞ ፓርኩ ደረቅ ወቅቶችን ያስተናግዳል፡፡ ፓርኩ ትናንሽ ሃይቆች በውስጡ ሲይዝ፣ ቡሎ፣ ከበሪላ፣ ሽታ እና ጮፎሬ ሃይቆች አብነት ሆነው ይጠቀሳሉ፡፡ በርካታ ወንዞችንም እንዲሁ በውስጡ ይዟል፡፡ ወደ 49 የሚጠጉ ወንዞች ከፓርኩ በመነሳት ወደ ኦሞ ወንዝ ይገባሉ፡፡ የአሳ ዝርያዎች፣ ፍል ውሃዎች፣ ፏፏቴዎች እና ዋሻዎችን የተቸረ ውብ የተፈጥሮ ፀጋ ባለቤት ነው፡፡ በተጨማሪም 37 ዓይነት ትላልቅ አጥቢ እንስሳት እና 237 የአዕዋፋት ዝርያዎች መገኛም ነው። ከአጥቢ እንስሳት መካከል የአፍሪካ ዝሆኖች፣ ጉማሬ፣ ጎሽ፣ አንበሳ፣ ነብር፣ አምባራይሌ፣ የተለያዩ የዝንጀሮ ዝርያዎች እና ከርከሮ ይገኙበታል፡፡ ጨበራ ጩርጩራ ብሄራዊ ፓርክ በ1997 ዓ.ም በብሄራዊ ፓርክነት እንደ ተቋቋመ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ፓርኩ የብዝሃ-ሕይወት እና የአስደማሚ የተፈጥሮ ሃብት ባለቤት በመሆኑ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ከሚገኙ የቱሪዝም መዳረሻዎች ዋነኛው ሆኖ እያገለገለ እንደሚገኝ ከደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ኮሙኒኬሽን የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
ዘመናዊነት እና አይበገሬነት የተጋመዱባት የአፍሪካ የልብ ምት - አዲስ አበባ
Dec 12, 2024 868
አዲስ አበባ ለፈተናዎች አልበገርም ብላ የለውጥ እና የሽግግር ምልክት ሆናለች ይላሉ የደቡብ አፍሪካው ብሔራዊ የትምህርት አገልግሎት ተቋም ዳይሬክተር ጀነራል ቡሳኒ ንካዌኒ። በደቡብ አፍሪካው ጋዜጣ እና የበይነ መረብ ዜናዎች አሰራጭ ዴይሊ ማቭሪክ ላይ የመዲናዋን ለውጥ በማድነቅ በከተቡት የግል አስተያየት አዲስ አበባ ለውጥ እንዳዘገመባቸው ወይም ባሉበት እንደቆሙት እንደ ደርባን፣ ሉዋንዳ፣ ኪንሻሳ እና ሞምባሳ ከተሞች አይደለችም ይላሉ። ተራራማ ከተማ ሲሉ የገለጿት አዲስ አበባን የተስፋ ተቀርኖዎችን እምቢኝ በማለት የራሷን ማንነት በራሷ መንገድ እየቀረጸች መሆኗን ይገልጻሉ። ተስፋ መቁረጥ ልክ እንደ በረ ቀልጦ ከተማዋ ወደ ታላቅነት የመቀየር ጉዞ ላይ እንደምትገኝም አመላክተዋል። አዲስ አበባ ታሪኳን እና የአፍሪካ ብርሃን የመሆን ሕልሟን አስታርቃ በሰሜናዊ እና ደቡባዊ የዓለም ንፍቀ ክበቦች ውስጥ ካሉ ጉምቱ ከተሞች የስሪት ሰንሰለት ሰብራ ራሷን ነጻ አውጥታለች። ቡሳኒ ንካዌኒ አዲስ አበባ ሁሌም የብርሃን ምንጭ ናት ይላሉ። አዲስ አበባ ከተቆረቆረችበት እ.አ.አ በ1886 ዘመን እስከ አሁን የነጻነት እና አንድነት ምልክት ሆና ቀጥላለች በማለትም ገልጸዋታል። በሰማይ ጠቀስ ሕንጻዎቿ መዲናዋ የራሷን ትርክት እየቀረጸች ነው ያሉት ፀሐፊው አዲስ አበባ ልዩ ያደርጋታል ያሉትን ሀሳብ በዚህ መልኩ ያስቀምጣሉ። “አዲስ አበባ ልክ እንደ ካይሮ የስማርት ከተሞች ልማት ሰው ሰራሽነት ማንነቷን ያነጠፈባት ወይም ልክ እንደ ኬፕ ታውን ሀብታሞች ድህነት ያለበትን ከተማ እንደቀየሩትና የከበርቴዎች እንክብካቤ የሚደረግላት ከተማ አይደለችም፤ ይልቁንም ድፍረት የተሞላበትን እሳቤ በመተግበር ቀስ በቀስ ግርማ ሞገሷንና ውበቷን እየገለጠች ያለች ከተማ ናት” ሲሉ ይገልጻሉ። የአዲስ አበባ ለውጥ ተጨባጭ ነው አሮጌ ሕንጻዎች በግዙፍ ሕንጻዎች መተካት ጀምረዋል፤ የመሰረተ ልማቱ ግንባታ፣ ከተማዋን የማስተሳሰር ስራ እና የትራንስፖርት አገልግሎቱ ለውጥ እያሳየ መምጣቱን መስክረዋል። ማራኪ የእግረኛ መንገዶች፣ የአደባባዮች ውበት፣ የትራፊክ መብራቶች እና ሌሎች የሚታዩ ለውጦች አዲስ አበባ የለውጥ ድባብ እንድትፈጥር ማድረጉን ይናገራሉ። በከተማዋ ያሉ አስገራሚ ለውጦች በየቦታው ቆም ብለህ አየር እየወሰድክ ነገሮችን በጥሞና ለመመልከት ይጋብዛል ሲሉም አክለዋል። ቡሳኒ ንካዌኒ በአዲስ አበባ ለውጥ የተደመሙበትን የግል ምልከታ ማንሳታቸውን በመቀጠል አዲስ አበባ የተለወጠችው በመሰረተ ልማቷ እና በኢንዱስትሪ ልማቷ ብቻ አይደለም በሕዝቧ ጭምር እንጂ በማለት ከትበዋል። የመዲናዋ ነዋሪዎች ልባቸውን በኩራት ሞልተው በእነዚህ መንገዶች ላይ ይንቀሳቀሳሉ። ውበትን ያየሁት የከተማው መሰረተ ልማቶች ላይ ብቻ አይደለም ሕዝቡ ላይም እንጂ ይላሉ። ነዋሪዎቹ የከተማዋ የለውጥ መንፈስ ተጋብቶባቸዋል። በተንቀሳቀስኩባቸው ቦታዎች የሕዝቡ ውበት፣ መስተጋብር፣ ባህል እና ሰው አክባሪነት እውነትም አዲስ አበባ ምድረ ቀደምት ናት እንድል አስገድዶኛል በማለትም ይገልጻሉ። ነዋሪዎቿ መንፈሳዊ እና ውስጣዊ ውበታቸው ማራኪ ነው ይላሉ በአስተያየታቸው። ለንካዌኒ አዲስ አበባ ከተማ ብቻ አይደለችም የብዙ ነገር ምልክት ናት። የአፍሪካ ሕብረት እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ተቋማት ማዕከል ጭምር እንጂ። ማዕከላዊቷ አዲስ አበባ የአፍሪካ መሪዎች የቀድሞው የአፍሪካ አንድነት ድርጅት ከመመስረት አንስቶ እስከ አሁን በርካታ ቁልፍ ውሳኔዎችን ለማሳለፍ ይሰበሰቡባታል። እንደ ኒካዌኒ ገለጻ አዲስ አበባ የፓን አፍሪካኒዝም ሀሳብ ተጸንሶ የተወለደባት ከተማ መሆኗ የሚያጠያይቅ አይደለም። ቀጣናዊ ፍላጎቶችና ፉክክሮች፣ ብሔራዊ ጥቅሞች እና የሀሳብ ተቃርኖዎች ያላቸውን አካላት በሙሉ አቅፋ ይዛለች። ይህም የባለ ብዝሃ ወገን ዲፕሎማሲ መናህሪያ እና ምልክት ያደርጋታል በማለትም ገልጸዋታል። ከሁሉም የዓለም ክፍሎች ዲፕሎማቶች አዲስ አበባ ይከትማሉ፤ ሰላም፣ ኒዎ ኮሎኒያሊዝም፣ ጸረ-ኢምፔሪያሊዝም፣ ልማት እና ሌሎች ግዙፍ አጀንዳዎችን በሻንጣቸው ይዘው መጥተው ይነጋገሩባታል። አጀንዳ 2063 የአፍሪካ እና ቀጣናዊ ትብብርን ማሳኪያ የጋራ ቃልኪዳን ሰነድ ነው። የአፍሪካውያንን እድገት እና ብልጽግና ሕልም በውስጡ አቅፎ ይዟል። ይሄ አጀንዳ በየጊዜው በአፍሪካ መዲናዋ አዲስ አበባ ቃል ኪዳን ይታደስባታል። አዲስ አበባ ከመሰብሰቢያነት ባለፈ የአንድነት ማቀጣጠያ ስፍራ፤ የአፍሪካ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ ሕልሞች መልክ የሚይዝባት እምብርት ነች ሲሉም ንካዌኒ አድናቆታቸውን ይገልጻሉ። አዲስ አበባ ስሟ እንደሚናገረው አዲስ ናት ሁሌ እንደአዲስ የምትፈካ አበባ ናት፤ ደማቅ ውበቷ ዘመናት የማይገድቡት እና የማይለውጡትም ጭምር። የአፍሪካ ታሪክ ተናጋሪ የሆነችው አዲስ አበባ አበቦቿ ደርቀውም ሆነ ረግፈው አያውቁም ሁሌም እንደ አዲስ ይታደሳሉ ሲሉ ጥንካሬዋን ያነሳሉ። አዲስ አበባ ለበርካታ ተፈጥሯዊ እና ሰው ሰራሽ ችግሮች ሳትበገር በማንነቷ ቀጥላለች ያሉት ንኮዌኒ መዲናዋ ትናንቷን ሳትረሳ ከዘመናዊነት ጋር ተጣምራ ጉዞዋን ቀጥላለች ብለዋል። በአዲስ አበባ የወጣው ፀሐይ የመዲናዋን መንገዶች ብቻ የሚያፈካ ሳይሆን ለመላ አፍሪካ መጻኢ ጊዜ ብሩህ መሆንን የሚያበስር ጭምር እንጂ ይላሉ። አዲስ አበባ፤ አስገራሚ የመንገድ መብራቶቿ፣ በየጊዜው እየፈኩ ያሉት ዛፎች፣ ጨዋ ሕዝቦቿ እና እያደጉ የመጡት ሕልሞቿ ለራሷ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ሕልም ስኬት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አላት የሚል እምነት ዳግም እንዲጣልባት አድርጓል ሲሉም አድናቆታቸውን ገልጸዋል። አዲስ አበባ ለውጧ የሚያሳምን፣ አቅምን የሚፈትሽ እና ራስህን እንድትለውጥ የሚያደርግ ነው ሲሉም ገልጸዋታል። ከተማዋ በብዝሃ እድገት አዲስ ምዕራፍ ውስጥ የምትገኝ ከተማ ናት፤ አዲስ አበባ የሆነችው በስሟ ብቻ ሳይሆን በአዲስ መንፈሷም ጭምር ነው በማለትም አድናቆታቸውን ችረዋታል። አዲስ አበባ ለውጥን አርግዛ አዲስ ማንነቷን ልትወልድ ተቃርባለች የሚሉት ጸሀፊው፤ የከተማዋ ውበት ያረፈው በአይበገሬነቷ እና በያዘችው ተስፋ ላይ ነውም ይላሉ። ቡሳኒ ንካዌኒ በዴይሊ ማቭሪክ ላይ የአዲስ አበባን ለውጥ አስመልክተው ያሰፈሩትን ጽሁፍ በድንቅ አገላለጽ ይቋጩታል። “አዲስ አበባ አንቺ ሁሌም የአፍሪካ ከተማ ልብ ሆነሽ ትቀጥያለሽ፣ ሕያዊቷ አዲስ አበባ እንዳለቅስ አታድርጊኝ፣ አዲሱ የዘመናዊነት የፍቅር ጊዜያችን ሁሌም ጸንቶ ይቀጥላል” ዘመናዊነት እና አይበገሬነት የተስማሙባት እና የተጋመዱባት የአፍሪካ የልብ ምት የሆነችው ከተማ፤ አዲስ አበባ በማለትም ጭምር።
ግብርናቸውንም፤ የኑሮ ዘይቤያቸውንም ያዘመኑት ብርቱው አርሶ አደር -ገብሩ ታፈሰ
Nov 8, 2024 1932
አርሶ አደር ገብሩ ታፈሰ በብርቱ አራሽነታቸውና በሞዴል አምራችነታቸው በቀዬው ማህበረሰብ ዘንድ ይታወቃሉ-በተለይ በበቆሎ ምርታቸው። አቶ ገብሩ በደጃቸው እና እርሻ ማሳቸው ላይ ሁሉን አቀፍ የግብርና ስራዎችን ይከውናሉ። ነገር ግን የተራቆተ ገላጣማ ማሳቸውን ወደ ፍሬፍሬ ደን ይለውጣሉ ብሎ የጠበቀ የአካባቢው ነዋሪ አልነበረም። በጉራጌ ዞን አበሽጌ ወረዳ የአብኮ ቀበሌ ነዋሪው አርሶ አደር ገብሩ ታፈሰ ግን በብርቱ ጥረታቸው አደረጉት። ከጥቂት ዓመታት በፊት ጀምረው ወንዝ ዳር የሚገኘውን የተራቆተ ማሳ በመንከባከብና ተገቢውን የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ስራ በመስራት ቀስ በቀስ ወደ አትክልትና ፍራፍሬ ማሳ ለወጡት። ከሶስት ዓመታት በፊት የጀመሩት የፍራፍሬ ልማት ዛሬ ከራሳቸው ፍጆታ አልፎ ምርታቸውን ለገበያ እያቀረቡ ነው። በመኸር ሰብል ብቻ ላተኮረው የአካባቢው ማህበረሰብም የተሞክሮ ማዕከል በመሆን ሙዝን ጨምሮ በስፍራው ያልተለመዱ አትክልቶችና ፍራፍሬ አይነቶች እንዲስፋፉ በማድረግ ዐይን ገላጭ ሆነዋል። "ከሁለት ዓመታት ወዲህ ባየሁት የተትረፈረፈ ምርት እስከዛሬ ማሳዬን አልምቼ ባለመጠቀሜ በጣም ይቆጠኛል" ይላሉ። አቶ ገብሩ ማሳቸው ብቻ ሳይሆን ደጃቸው የብርቱ ገበሬ አሻራ ይነበብበታል። በመኸር በጋ መስኖም ሰብሎችን በስፋት ከማምረት ባለፈ የሰንጋ በሬ ያደልባሉ፤ የሌማት ቱርፋት ግብዓት የሆኑ ከዶሮ እስከ ወተት ላም ያረባሉ፣ የራሳቸው ወፍጮ ቤት አቋቁመው ይሰራሉ። በበሬ ብቻ ሳይሆን በትራክተር በመታገዝ ሰፋፊ እርሻ የሚያለሙ አርአያ ሰብ ናቸው። አርሶ አደር ገብሩ ከራሳቸው አልፈው ሌሎች የቀያቸው ነዋሪዎች በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት እንዲሰማሩ ተሞክሯቸውን ያጋራሉ። አቅማቸው በፈቀደው ልክም የግብርና ግብዓት እገዛ ያደርጋሉ። በመንግሰት በተሰጠው ትኩረት በመመራት እና የእርሳቸውን ፈለግ ተከትለው በፍራፍሬና ሌሎች ልማቶች የተሰማሩ አርሶ አደሮች ውጤታማ መሆናቸውን ያነሳሉ። ብርቱው አርሶ አደር ገብሩ ታፈሰ ዕውን ያደረጉት ታዲያ የተቀናጀና የዘመነ ግብርና ስራን ብቻ አይደለም። ይልቁኑም ባዘመኑት ግብርና በመመራት የገጠር የኑሮ ዘይቤያቸውንም አዘምነዋል። የሰውና እንስሳት የመኖሪያ ቤት በመለየት፣ መጸዳጃ ቤት በመገንባትና የቤት አያያዝን በማሻሻል በምሳሌነት ይጠቀሳሉ። "ምንም የአርሶ አደር ቤት ቢሆን የተሻለና ፅዱ አኗኗር እንከተላለን" ሲሉ የገጠር ኮሪደር ዓላማ ጋር የሚጣጣም ስራቸውን ይገልጻሉ። "ከጨውና ዘይት በስተቀር የምንገዛው የለም" ከምግብ ዋስትና ማረጋገጥ ባሻገር ከገጠር እስከ ከተማ የተሻለ ሀብት የማፍራት፣ ልጆችን የማስተማርና ደስተኛ የቤተሰብ ሕይወት የመምራት ህልም እንዳሳኩ ይገልፃሉ። የአበሽጌ ወረዳ ግብርና ፅህፈት ቤት ኃላፊ አብዱልከሪም ናስር እንደሚሉት አርሶ አደር ገብሩ የተራቆተ መሬትን እንዲያገግም በማድረግና በአትክልትና ፍራፍሬ ልማት ያመጡት ለውጥ ለሌሎች አርዐያ የሚሆን ነው። የነ አቶ ገብሩ አካባቢ በቦቆሎ እንጂ በሙዝ ፍራፍሬ ልማት እምብዛም እንደማይታወቅ አስታውሰው፤ በከልሉ በመጀመሪያ ዓመት 30፣ በሁለተኛው ዓመት 40 እና በሶስተኛው ዓመት 30 የፍራፍሬ ችግኞችን የመትከል ኢኒሼቲቭ ግን አርሶ አደሮችን ወደ ፍራፍሬ ልማት በማስገባት የነበረውን አስተሳሰብ መለወጥ እንደተቻለ ጠቁመዋል። አቶ ገብሩን ጨምሮ በወረዳቸው ለገጠር ኮሪደር ልማት ምሳሌ የሚሆኑ አርሶአደሮች እንዳሉ በማውሳት፣ አትክልትና ፍራፍሬ ልማትን በሁሉም ዘንድ ተደራሽ ለማድረግ ትኩረት መደረጉን ገልጸዋል። በአረንጓዴ አሻራ፣ በሌማት ቱርፋት፣ ውብና ፅዱ አካባቢን በመፍጠር እንዲሁም ዘመናዊ የኑሮ ዘይቤን በማስፋት የገጠር ኮሪደር ልማትን ዕውን ለማድረግ እየተሰራ መሆኑንም ነው የተናገሩት።
ከደመና በላይ የሚቀዝፈው የኢትዮጵያ ትዕምርት
Nov 5, 2024 1801
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተቋም ብቻ አይደለም የአገር ምልክት ጭምር እንጂ። ከኢትዮጵያ አልፎ የአፍሪካውያን ኩራት የሆነ አድማስ ተሻጋሪ ስመጥር ተቋም ነው። በውድድር የከበዳቸውን በሴራ ለማሳካት ብዙዎች የማሱለትን ጉድጓዶቹን እየደፈነ ፈተናዎችን በጥበብ እየተሻገረ የትውልድ ቅብብሎሽ ገናናነቱን አስጠብቆ 78 ዓመታትን ዘልቋል። በዚህም ብዙ ክብር ብዙ ሞገስ አግኝቷል። ተቆጥረው የማያልቁ የምርጥ አየር መንገድነት ክብሮችን ተቀዳጅቷል። አስተማማኝነቱ እና የላቀ የደንበኞች አገልግሎቱ በአፍሪካ ግንባር ቀደም፣ በዓለም ደግሞ ተጠቃሽ ሆኖ እንዲቀጥል አስችለውታል። በ1938 ዓ.ም የተቋቋመው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዚያው ዓመት የመጀመሪያ በረራውን ወደ ካይሮ ያደረገ ሲሆን ትንሿ ዳግላስ (Douglas C-47 Skytrain) የመጀመሪያዋ የአየር መንገዱ አድማስ ዘለል አውሮፕላን ነች። በዚያው ዓመት አቅሙን በፍጥነት አሳድጎ መዳረሻውን በአፍሪካና ከአፍሪካ ውጭም ማስፋት ችሏል፡፡ የዕድገት ፍጥነቱን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ እንደ ቦይንግ 720፣ 727፣ 737፣ 757፣ 767፣ 777 ያሉ ትላልቅና የላቀ ምቾት ያላቸው አውሮፕላኖች ባለቤት መሆን ቻለ። አየር መንገዱ የግዙፉ የአየር መንገዶች ጥምረት ስታር አሊያንስ አባል በሆነ በጥቂት ዓመታት ውስጥ በነዳጅ ቆጣቢነቱ የሚታወቀውን Airbus A350 XWB አውሮፕላን በመግዛት የመጀመሪያው የአፍሪካ አየር መንገድ ሆኗል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በቅርቡ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በሰጡት ማብራሪያ አየር መንገዱ 124 አውሮፕላኖችን ለመግዛት ማዘዙን መናገራቸው ይታወቃል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን አየር መንገዱ በዓመት እስከ 130 ሚሊየን መንገደኞችን ማስተናገድ የሚችል ግዙፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመሩም እንዲሁ፡፡ ይህም የኢትዮጵያ አየር መንገድን በአፍሪካ ትልቁ የአውሮፕላን ባለቤት ብቻ ሳይሆን ግዙፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ያለው ተቋም ያደርገዋል፡፡ አየር መንገዱ እያስመዘገበ ያለው ስኬት የኢትዮጵያ የማንሰራራት ዘመን ማሳያ ሲሆን፤ በጀት ዓመቱ በአገልግሎት ዘርፍ 7 ነጥብ 1 በመቶ እድገት ለማስመዝገብ የተቀመጠውን ግብ ለማሳካት ሚናው የጎላ ነው፡፡ በአፍሪካ በቀዳሚነቱ እየገሰገሰ ያለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዘመናዊ አውሮፕላኖችን በየጊዜው ለአፍሪካ ማስተዋወቁን ቀጥሎበት በትላንትናው ዕለት የኤ350-1000 አውሮፕላን ከኤር ባስ ኩባንያ ተረክቧል። Airbus A350-1000 የላቀ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል ቴክኖሎጂ የተገጠመለት አውሮፕላኑ በአየር መንገዱ ምድረ ቀደምት (Ethiopia land of origins) የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል፡፡ ይህም አየር መንገዱ ለመንገደኞች ምቹ አገልግሎት የመስጠት አቅሙ እንዲጨምር ያደርጋል። የኢትዮጵያ አየር ኃይል ዋና አዛዥና የኢትዮጵያ አየር መንገድ የቦርድ ሰብሳቢ ሌተናል ጄኔራል ይልማ መርዳሳ፤ በዚሁ ወቅት እንደተናገሩት ኢትዮጵያ አጠቃላይ ሀገራዊ ሪፎርም ላይ ትገኛለች። በአፍሪካ የመሪነት ሚናውን እየተወጣ ያለው የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአህጉሪቷ ኢኮኖሚ ትስስርን በመፍጠር የማይተካ ሚና እየተጫወተ መሆኑን ገልጸዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ዋና ስራ አስፈጻሚ መስፍን ጣሰው በበኩላቸው ፣የኤ350-1000 አውሮፕላን ወደ ገበያው መግባት አየር መንገዱ የተያያዘውን ፈጣን እድገት በላቀ ደረጃ ለማሳለጥ ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን አንስተዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአፍሪካ አዳዲስ አውሮፕላኖችን በማስገባት ፈር ቀዳጅ መሆኑን በማንሳት፣ ኤ 350-1000 አውሮፕላንም በአየር መንገዱ ታሪክ ትልቅ ስኬት መሆኑን አክለዋል። የኤር ባስ ኩባንያ ዓለም አቀፍ ዋና ስራ አስፈጻሚ ውተር ቫን ዌርሰች በበኩላቸው ይህ በአፍሪካ የመጀመሪያ የሆነው የኤ350_1000 አውሮፕላን ለኢትዮጵያ አየር መንገድ ራዕይ 2035 ስኬት ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን ገልጸዋል። በቀጣይ ጊዜያትም ኩባንያው ከኢትዮጵያ አየር መንገድ ጋር በትብብር ለመስራት ትልቅ ፍላጎት አለው ብለዋል። የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአሁኑ ወቅትም ባሉት 147 አውሮፕላኖች 139 ዓለም አቀፍና 22 የሀገር ውስጥ የበረራ መዳረሻዎችን እየሸፈነ ይገኛል። አየር መንገዱ በዓመት እስከ 130 ሚሊየን መንገደኞችን ማስተናገድ የሚችል ግዙፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመሩም እንዲሁ። የኢትዮጵያ አየር መንገድ ብሄራዊ ኩራትነቱ፣ የአገር ትዕምርትነቱ፣ የፓን አፍሪካ ምሳሌነቱ እና ዓለምአቀፍ ተወዳዳሪነቱ በጉልህ እየተንጸባረቀ ከደመና በላይ መቅዘፉን ይቀጥላል።
"ጊፋታ" - የአዲስ ተስፋ ብስራትና የአብሮነት ተምሳሌት!
Sep 22, 2024 2696
(በፋኑኤል ዳዊት ከሀዋሳ ኢዜአ ቅርንጫፍ) "ዮዮ ጊፋታ" ለጊፋታ በዓል እንኳን አደረሳችሁ አደረሰን ማለት ነው። ዮዮ ጊፋታ በሚሰማበት ጊዜ በወላይታ ተወላጆች ዘንድ የሚፈጠረው ወደአዲስ ዘመን መሻገርና አዲስ ተስፋን የሚጭር ስሜት ነው። የዮ ጊፋታ ወላይታዎች አዲሱን ዓመት ለመቀበል በአዲስ ተስፋና ብስራት ከያሉበት ተሰባስበው በአብሮነት የሚያከብሩት በዓል ነው። በዓሉ ያለፈውን ዓመት ስኬትና ክፍተት በመገምገም የሚመጣውን ዘመን በተሻለ እምርታ ለመቀበል በሚያስችል የመንፈስ መነቃቃትም ይከበራል። "ጊፋታ" የአዲስ ተስፋ ብስራትና የአብሮነት ተምሳሌት የሆኑ ልዩ ቀለማትን አካቶ በአብሮነት የሚከበር በዓልም ነው። የወላይታ ተወላጆች በያሉበት ዓመቱን ሙሉ በሥራ ካሳለፉ በኋላ ወደየአካባቢያቸውና ወደወላጆቻቸው ተመልሰው በዓሉን በአብሮነት ያከብሩታል። ሰላምና አንድነታቸውን ለማጠናከር በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ ከአባቶችና ወላጆች እንዲሁም ከሀገር ሽማግሌዎች ምክርና ምርቃት የሚወሰድበት ነው። በመሆኑም ጊፋታ በየዓመቱ በተወላጆቹ ዘንድ በጉጉት ይጠበቃል። በዓሉ ወደ መልካም ነገር የመሸጋገርያ ቀን ተደርጎም ይወሰዳል። በተለይ በዓሉ አዲስ ዘመንን መቀበልን ስለሚያበስር ይቅርታ፣ አብሮነት እንዲሁም በጋራ ተሰባስቦ ማክበር የበዓሉ ልዩ ዕሴቶች ናቸው። በመሆኑም በጊፋታ በዓል ወቅት የተጣላው ይታረቃል። ሰላምን ያወርዳል። አሮጌውን ዓመት በመሸኘት አዲሱን ዓመት በተስፋ ብርሃን መቀበል የተለመደ ነው። ወላይታዎች በሚያካሂዱት የዘመን መቁጠሪያ መሰረት የሚከበረው "ጊፋታ" ታላቅ፣ በኩር ወይም የመጀመሪያ የሚልና መሰል ትርጓሜ አለው። በተለያዩ የጊዜ ክፍልፋዮች ዘመንን በመቁጠር የበዓሉ ቀን የሚወሰን ቢሆንም የክረምት ጭጋግ መውጫ ወቅት ተከትሎ በዓሉ ይከበራል። በወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ የታሪክና ቅርስ ትምህርት ክፍል መምህርና ተመራማሪ ዶክተር አበሻ ሽርኮ ጊፋታ የመጀመሪያ እንደማለት ሲሆን በዓሉም የወላይታ አባቶች እንዳስቀመጡት የክረትም ጭጋግ ወቅት መውጣትና ብርሃን የሚታይበት ወቅትን መነሻ አድርገው እንደሚያከብሩት ተናግረዋል። ዶክተር አበሻ እንዳሉት በዓሉ ከአሮጌው ወደ አዲሱ ዓመት የሚሸጋገሩበት፣ አዲስ ተስፋ የሚሰነቅበት እንዲሁም ለልማትና ለሰላም የሚነሱበት በመሆኑ “የሰላም ተምሳሌት” ተደርጎ ይከበራል። በበዓሉ የተጣላ ይታረቃል፣ በክረምቱ ምክንያት የተጠፋፋም ይገናኛል፣ አቅም ያለው የሌለውን ይደገፋል። በዓሉ ተሰባስበው በጋራ ማደግ እንደሚቻል የሚመከርበት ሲሆን ተበድሮ ያልከፈለ ካለም ችግሩ ተመክሮበት መፍትሄ ይሰጠዋል። በአጠቃላይ በዓሉ አዲሱን ዓመት በተስፋና በአብሮነት ለመቀበል ስንቅ የሚያዝበት ጭምር ነው። ጊፋታ ሲከበር በዓመቱ ሰርቶ ስኬታማ የሆነና በተሻለ የመራ ሲወደስ በአንጻሩ ውጤታማ ያልሆነው ከሌላው ተሞክሮ የሚወስድበት መሆኑን የተናገሩት ዶክተር አበሻ፣ በዓሉ ዕሴት ለማህበራዊና ኢኮኖሚ እንዲሁም ሰላምን በመገንባት ልማትና ብልጽግናን ለማፋጠን ወሳኝ መሆኑን ነው የተናገሩት። የወላይታ ዞን ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ አቶ ምህረቱ ሳሙኤልም በበኩላቸው ጊፋታ በወላይታዎች ዘንድ ከዘመን ወደዘመን ከመሻገር ባለፈ የአዲስ ተስፋና ለቀጣይ የልማት ሥራዎች መሰረት የሚጣልበት ነው ይላሉ። በተለይም ጊፋታ ሰርቶ መለወጥንና በራስ ባህል መኩራትን እንደሚያበረታታ ጠቁመው ለዚህም ተወላጆቹ የመንፈስ ጥንካሬን እንደሚላበሱ ነው የገለጹት። በጋራ የሚመከርበትና የስኬት መነሻ ተደርጎም ይወሰዳል። በወላይታ ዘንድ ጊፋታ ሲደርስ ልዩነትን ፈትቶ እርቅ ማውረድ ቅድሚያ የሚሰጠው ጉዳይ ነው። አቶ ምህረቱ እንደሚሉት ይህም በዓሉ የአብሮነትና የሰላም እሴቶች እንዳሉት ማሳያ ነው። በዓሉ ለሰላም ፣ አብሮነትና ልማትን ለማጠናከር ካለው ፋይዳ በመነሳት የአሁኑ ትውልድ ሀገር በቀል ዕውቀቱንና ትውፊቱን ከመጠቀም በላፈ ለትውልድ ጠብቆ እንዲያቆየው ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ገልጸዋል። በአሁኑ ወቅት የዞኑ አስተዳደር ከወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሰቲና የቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን ጋር በመቀናጀት የጊፋታ በዓል ባህላዊ እሴቶች ይበልጥ እንዲተዋወቁና በዓሉም ዓለም አቀፍ ቅርስ ሆኖ በዩኔስኮ በማይዳሰሱ የሰው ልጅ ወካይ ቅርሶች መካከል እንዲመዘገብ ለማስቻል ተስፋ ሰጪ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል። የሶዶ ከተማ ነዋሪ ወይዘሮ አበበች ኤካሶ እንዳሉት ጊፋታ የሰላምና ዕርቅ እንዲሁም ቤተሰብ፣ ወዳጅ ዘመድ እና ጎረቤት የሚጠያየቅበት በዓል ነው። በዚህም አብሮነትና ሰላም ይጠነክራል፤ በሂደቱም አንዱ ከሌላው የስኬት ልምድን ይቀስማል፤ ከድክመቱም ይማራል። በበዓሉ ላይ ከሚከናወኑ ሁነቶች መካከል በዋናነት የአባቶች ምርቃትን የጠቀሱት ወይዘሮ አበበች ወጣቶች ነገአቸው የሰመረ እንዲሆን በአባቶች ይመረቃሉ። ልጆች በበዓሉ ወቅት ወደቤተሰቦቻቸው እንዲሰባሰቡ ከሚያደርጋቸው ምክንያቶች አንዱ ይሄው የምረቃ ሥነስርአት እንደሆነም ነው የገለጹት። ምረቃው ሲካሄድ በዓመቱ ሰርቶ የተሳካለትን በማሞገስና ያልተሳካለትን ደግሞ በመምከር ለቀጣይ በአዲስ ተስፋ ለስራ እንዲነሳሱ ይደረጋል። በመሆኑም “ጊፋታ የአዲስ ተስፋ ብስራት“ ተደርጎ ይወሰዳል። በምድር ስትኖር “ወልደህ ከወግ ማዕረግ ለማድረስ፣ ሰርተህ ለስኬት መብቃትና ልቀህ መታየት ትመኛለህ ያሉት ወይዘሮ አበበች ጊፋታ ከእነዚህ ሁሉ ጋር የተያዘ ስለሆነ በተለይም ድህነትና ኋላ ቀርነትን ለማሸነፍና በራሱ የሚኮራ ትውልድ ከማፍራት አንጻር ልዩ ትርጉም እንዳለው ነው የገለጹት። የወላይታ ሀገር ሽማግሌ አቶ ሚልክያስ ኦሎሎ በበኩላቸው እንዳሉት የጊፋታ በዓል የአዲስ ተስፋ ብስራት ነው። እሳቸው እንዳሉት የበዓሉ ዕሴት አዲስ ዘመንን በቂምና ቁርሾ መቀበልና መሻገር አይቻልም። በመሆኑም በግለሰብ ብቻ ሳይሆን በመንግስትና ህዝብ መካከል እንኳ ችግሮችና አለመግባባቶች ቢኖሩ በዓሉን የሚቀበሉት ተነጋግሮ ችግሮችን በመፍታትና በዕርቅ ነው። ይህም ቀጣይ ጊዜን በአብሮነትና በሰላም ለማሳለፍ ጉልህ ሚና አለው። ለእዚህም ነው ጊፋታ የአዲስ ተስፋ ብስራትና የአብሮነት ተምሳሌት የሚያደርገው። "በዓሉ ዓመቱን ሙሉ በተለያዩ ክዋኔዎች የሚታሰብ ነው" ያሉት አቶ ሚልክያስ በተለይም ለሰላምና ለአብሮነት የሚሰጠው ቦታ ልዩ መሆኑን ነው የገለጹት። ይህም ሰላማዊ አካባቢ በመፍጠር ዜጎች ልማት ላይ እንዲያተኮሩ ያደርጋል ባይ ናቸው። የወላይታ ዞንም ሰላማዊ ሆኖ ልማቱ ላይ ብቻ እንዲያተኮር የጊፋታ ዕሴት የጎላ አስተዋጾ እንዳለው ጠቁመው፣ በአሁኑ ወቅት ትውልዱ ባህሉን ይበልጥ እንዲያውቅና እንዲረዳ እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች መጠናከር እንዳለባቸው ተናግረዋል። የወላይታ ብሔር የዘመን መለወጫ "ጊፋታ" በዓል በተለያዩ ክዋኔዎች ታጅቦ በድምቀት እየተከበረ ነው። ዮዮ ጊፋታ!
መውሊድ - የአብሮነትና የሰላም ተምሳሌት
Sep 15, 2024 2592
መውሊድ አል-ነቢ፣ መውሊድ አን-ነቢ፣ መውሊዲ ሸሪፍ፣ ሚላድ፣ ኢድ ሚላድ ኡን ነቢ፣ ኢድ አል-መውሊድ …ይህ ሁሉ የነብዩ መሐመድ (ሰዐወ) የልደት ቀን መጠሪያ ነው። መውሊድ የሚከበረው በረቢዓል አወል ወር በ12ኛው ቀን አንዳንድ ሀገራት ደግሞ በ17ኛው ቀን መሆኑ ይነገራል። መውሊድ በመኖሪያ ቤት፣ በመስጊድና በታላላቅ እስላማዊ ማዕከላት ነብዩ በተወለዱበት በረቢየል አወል ወር አሥራ ሁለተኛው ቀን፣ ወይም ነብዩ በተወለዱበት ወር ውስጥ በሚገኝ ሰኞ፣ ወይም በማንኛውም ወር በሚገኝ ሰኞ ቀን ይከበራል። ዘንድሮም 1 ሺህ 499ኛው የነብዩ መሐመድ (ሰዐወ) ልደት (መውሊድ) በዓል በትውፊቱ መሠረት በተለያዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶች “የሰላሙ ነብይ” በሚል መሪ ሃሳብ በድምቀት እየተከበረ ይገኛል። በዓሉ ''የሰላሙ ነብይ'' በሚል መሪ ሃሳብ መከበሩ ሰላም ያለውን ከፍተኛ ዋጋ ከማሳየትም በላይ በእስልምና ለሰላም የሚሰጠው ትኩረት ምን ያህል የገዘፈ እንደሆነ የሚያሳይ ነው። በመውሊድ በዓል የነብዩ ታሪክ፣ የእስልምና አመጣጥና ሀዲሶች ይነበባሉ። በተጨማሪም ቁርዓን በመቅራት፣ የውዳሴ ግጥሞችን በማቅረብ፣ ጣፋጭ ምግቦችን በማዘጋጀትና ለአቅመ ደካሞች ማዕድ በማጋራት እንዲሁም ስጦታ በመለዋወጥ ነው የሚከበረው። በገጠር የመውሊድ ሥርዓት በአብዛኛው ከሦስት ተከታታይ ቀናት በላይ የሚከበር ሲሆን በተለይ በቀደምት ታላላቅ እስላማዊ ማዕከላት በዓሉ በልዩ ውበት እና ድባብ ይከበራል። በብዙ አገሮች መውሊድ ሲከበር በጥንት ጊዜ የተጻፉ ሀይማኖታዊ ይዘት ያላቸው የግጥም መጽሐፍት የሚነበቡ ሲሆን፣ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ ሀገሮች ደግሞ በራሳቸው ሊቃውንት የተዘጋጁ የውዳሴ ግጥሞችን በዜማ በማቅረብ በዓሉን ያድምቃሉ። በግጥሞቹ ውስጥ ስለ ነቢዩ ውልደትና ዕድገት፣ ስለ ቤተሰቦቻቸው ታሪክ፣ ስለተለያዩ አስገራሚ ክንዋኔአቸው፣ ስለ አርቆ አስተዋይነታቸው፣ ስለታላቅነታቸው፣ ስለመጀመሪያው ራዕይ፣ ስለ ቀደምት ተከታዮቻቸው፣ ወዘተ ይዳሰሳል። መውሊድ ሲከበር ሰደቃ አለ፤ በዚህም ሀብታምና ድሃ ይገናኛሉ፤ የፈጣሪን ውዴታ በምጽዋዕት ከማግኘት ባሻገር የማኅበራዊ ግንኙነትና ትስስር ይጠናከራል። መውሊድ ወንድማማችነትና አብሮነት የሚያንፀባርቅበትም ነው። መውሊድ መንዙማ በስፋት ከሚተገበርባቸው በዓላት አንዱ ነው። መውሊድና መንዙማ ጥብቅ ትስስር አላቸው። መንዙማ ማመስገን ወይም ማወደስ ማለት ነው። ይዘቱም ፈጣሪ የሚመሰገንበት፣ ነቢዩ የሚሞገሱበት፣ የእስልምና ትምህርት የሚሰጥበት፣ ታላላቅ ሰዎች ገድላቸውና ተዓምራቸው የሚነገርበት፣ የተማፅኖ ጸሎት የሚደረግበት ነው። በኢትዮጵያ እነዚህ የመውሊድ ክንዋኔዎች በትግራይ ነጃሽ፣ በሆጂራ ፎቂሳ፣ በሰሜን ወሎ ዳና፣ በደቡብ ወሎ ጃማ ንጉሥ፣ በባሌ በድሬ ሸኽ ኹሴን፣ በጅማ በቁባ አባረቡ፣ በደንግላ እና በሌሎችም አካባቢዎች በስፋት ይከናወናሉ። የዘንድሮ ዓመት የመወሊድ በዓል የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት የተቋቋመበት 50ኛ ዓመት በዕለተ መውሊድ በመሆኑ በዓሉ ድርብ በመሆኑ በተለየ ዝግጅት ነው እየተከበረ የሚገኘው። የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ሥራ አስፈጻሚ አባልና የመውሊድ በዓል አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ ሸይኽ አብዱልሐሚድ አህመድ እንደገለጹት፤ የመጅሊሱን 50ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በአዲስ አበባ በታላቁ አንዋር መስጂድ የመውሊድ በዓል በተለያዩ ስርዓተ ክዋኔ በደማቅ መርሃ ግብር ተከብሯል። ከዚህም በተጨማሪ የረቢዕል አወል ወር እስኪጠናቀቅ ድረስ የሚሰጡ ትምህርቶችና ደዕዋዎች (ስብከቶች) “የሰላሙ ነቢይ፡” ከሚል መሪ ሃሳብ እንዲሆን በምክር ቤቱ የመውሊድ ዓቢይ ኮሚቴ ውሳኔ ተላለፎ ተግባራዊ እየተደረገ ይገኛል። በዚሁም መሰረት የሰላም ግንባታ ሥራዎችን በመደገፍ፤ ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ በማድረግ ህዝበ ሙስሊሙ አስተዋጽኦውን አጠናክሮ እንዲቀጥል የሚያስችለውን ብርታትና ቁርጠኝነት የሚሰንቅበት በዓል ሆኖ እየተከበረ መሆኑን አንስተዋል። የሰላምና የአብሮነት ምልክት ለሆነው ለዚህ መልካም ዓላማ መሳካት ያለ ልዩነት በጋራ በመተሳሰብ፤ በእዝነት የነብዩን መልካም ስራዎች መስራት እንደሚገባ አስረድተዋል። የሃይማኖቱ አባቶችም ከመዕመኑ ጋር በመሆን በጸሎት፣ ቁርዓን በመቅራትና ሐዲሶችን በማንበብ ለሀገር ሰላምና ለህዝቦች አንድነት መጸለይና በማስተማርን የየዕለት ተግባራቸው ሊያደርጉት እንደሚገባ አንስተዋል። በርግጥም የዘንድሮው የመውሊድ በዓል ድርብ በዓል ነው። መጅሊስ የተቋቋመው የዛሬ 50 ዓመት በመውሊድ ዕለት ነበርና። መልካም በዓል!
ለዘመናት ጥያቄ ምላሽ ሰጪው ጭላንጭል ተስፋ
Aug 8, 2024 2572
በትንሳኤ ገመቹ (ኢዜአ) የዛሬው የ76 ዓመት የዕድሜ ባለፀጋ ያኔ በለጋነታቸው፤ ዳገት፣ ቁልቁለት፣ ሜዳ ሳይመርጡ እንዳሻቸው በሚቦርቁበት፣ ሮጠው በማይጠግቡበት፣ ገና ታዳጊ ሳሉ በ13 ዓመት ዕድሜያቸው በደረሰባቸው የተሽከርካሪ አደጋ ነው ሁለት እግሮቻቸውን ያጡት። ይሁንና ይህ ጉዳታቸው ሳይበግራቸው በብዙ ውጣ ውረድና እልህ አስጨራሽ ትግል በትምህርታቸው እስከ ዩኒቨርሲቲ ድረስ መዝለቅ ችለዋል። እኚህ ሰው ካለሙበት ለመድረስ በርካታ ውጣ ውረዶችን አልፈዋል። ትውልድና ዕድገታቸው በአዲስ አበባ መሆኑ በተሽከርካሪ ወንበር (ዊልቼር) ድጋፍ ወደ ትምህርት ቤት የመሄድ ዕድልን ሰጥቷቸዋል፤ የሥራ ዓለምንም ተቀላቅለዋል። ይህ ስኬታቸው ግን እንዲሁ እንደዋዛ የተገኘ አልነበረም። የመዲናዋ የእግረኛም ሆኑ የተሽከርካሪ መሄጃ አስፓልት መንገዶች አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ያላደረጉ፤ ለዊልቼር መንቀሳቀሻ በቂ ቦታ የሌላቸውና አስቸጋሪ መሆናቸው እንቅስቃሴያቸውን በእጅጉ አክብዶባቸዋል፤ ለዓመታት በዊልቼር የተመላለሱባቸው ለእግረኛ እንኳን የማይመቹ የተቦረቦሩ፣ ወጣገባ፣ ዳገታማና ቁልቁለታማ መንገዶች ተጨማሪ የሕይወት ፈተናዎቻቸው ነበሩ። አዛውንቱ በታዳጊ፣ በወጣትነት እና በጉልምስናም ዕድሜያቸው በእጅጉ የፈተኗቸውን እነዚያን የስቃይ ጊዜያት “መቼም አልረሳቸውም” ሲሉ እንደ እርሳቸው የአካል ጉዳት የገጠማቸውን ሰዎች የዕለት ተዕለት ተግዳሮቶች ይገልጻሉ፤ አቶ አለበል ሞላ። ዓለም አቀፋዊ የአካል ጉዳተኝነት ሁኔታ በዓለም-አቀፉ የአካል ጉዳተኞች መብት ኮንቬንሽን አንቀፅ አንድ እንደተመለከተው አካል ጉዳተኝነት ከረጅም ጊዜ የአካል፣ የአዕምሮ ወይም የስሜት ህዋሳት እክል ጋር የሚኖሩና በአመለካከትና በአካባቢያዊ ጋሬጣዎች ምክንያት በማኅብረሰቡ ውስጥ ሙሉና ትርጉም ያለው ተሳትፎ በእኩልነት ማድረግ የማይችሉ ሰዎችን ያጠቃልላል። አካል ጉዳት ማለት፤ የአካል ክፍልን ማጣት ወይም የተግባር መገደብን የሚያመላክት ፅንሰ-ሀሳብ ነው። አካል ጉዳተኝነት ማለት ደግሞ ከሌሎች ሰዎች ጋር እኩል ተሳትፎ እንዳያደርጉ የሚያደርግ የአካል ጉዳት፣ የአመለካከት ችግርና አካባቢያዊ መሰናክሎች ድምር ውጤት ነው። በዓለም ላይ የተለያየ አይነት አካል ጉዳተኝነት የሚያጋጥም ሲሆን፤ ዓይነ-ስውርነት፣ መስማት መሳን፣ የአዕምሮ ዕድገት ውስንነት፣ ማየትና መስማት መሳን እንዲሁም ተደራራቢ የአካል ጉዳት ዋና ዋናዎቹ ናቸው። የዓለም ጤና ድርጅት እንደ አውሮፓዊያኑ አቆጣጠር 2023 ያወጣው መረጃ እንደሚያመላክተው 1 ነጥብ 3 ቢሊዮን ያህል ሰዎች የተለያየ አይነት የአካል ጉዳት ያጋጥማቸዋል። ይህ አሃዝ 16 በመቶ የሚሆነውን የዓለም ሕዝብ ቁጥር የሚወክል ነው። ይህም የአካል ጉዳት ከስድስት ሰዎች በአንዱ ላይ አለ ማለት ነው። እነዚህ ዜጎች ከአካል ጉዳተኝነት ጋር ተያይዞ የሚከሰቱ ተያያዥ የጤና እክሎች የሚያጋጥማቸው መሆኑንም መረጃው ያሳያል። ድብርት፣ አስም፣ የስኳር በሽታ፣ ስትሮክ፣ አላስፈላጊ የሰውነት ክብደት መጨመር፣ የአፍ ጤና እክልና ሌሎችም ተያያዥ በሽታዎች ከአካል ጉዳተኝነት ጋር ተያይዘው ከሚከሰቱት መካከል ይጠቀሳሉ። በዓለም ላይ ስለ አካል ጉዳተኝነት ያለው ስያሜ የተለያየ ነው። ለምሣሌ በተለያዩ አገራት ያለው ቴክኖሎጂ፣ የሰዎች አመለካከት፣ ከድጋፍ አሰጣጥና ከመሰረተ ልማት ተደራሽነት ጋር ተያይዞ ለአካል ጉዳተኝነት የሚሰጠው ስያሜ እንዲለያይ አድርጓል። ለአብነት ለዓይነስውራን ልዩ የዓይን መነፅርና ሌሎች አስፈላጊ ቁሳቁሶችን ማቅረብ በሚችሉ አገራት ዓይነስውራን እንደ አካል ጉዳተኛ አይታዩም። የአዕምሮ ዕድገት ውስንነት ያለባቸው ሕፃናት ወደ ትምህርት ቤት የማይሄዱት በወላጆቻቸው የተዛባ አመለካከትና ትምህርት ቤቶች ለልዩ ፍላጎት ማስተማሪያ ተገቢውን ቁሳቁስ ማሟላት ባለመቻላቸው እንጂ ሕፃናቱ መማር ስለማይችሉ ወይም ቢማሩ ስለማይለወጡ አይደለም። ይህን ማሟላት በቻሉ አገራት የአዕምሮ ዕድገት ውስንነት ያለባቸው ልጆች እንደ አካል ጉዳተኛ ሊቆጠሩ አይችሉም። በሌላ በኩል በተሽከርካሪ ወንበር (ዊልቼር) ለሚንቀሳቀስ ሰው ትምህርት ቤትም ሆነ ወደ ስራ ቦታ ለመሄድ የሚያዳግተው አካል ጉዳቱ ሳይሆን፤ ለመንቀሳቀስ የሚያስችል ምቹ ሁኔታ ሳይፈጠርለት ሲቀር ብቻ ነው። የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት የሳይንስና የባሕል ተቋም (ዩኔስኮ) መረጃ እንደሚያሳየው በታዳጊ አገራት 90 በመቶ አካል ጉዳተኛ ልጆች ትምህርታቸውን አይከታተሉም። እ.ኤ.አ 1998 ይፋ የሆነው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ጥናት የአካል ጉዳተኛ ጎልማሶች ዓለም አቀፋዊ የማንበብ ደረጃ ሦስት በመቶ ሲሆን የአካል ጉዳተኛ ሴቶች ደግሞ አንድ በመቶ ብቻ መሆኑን አመላክቷል። አካል ጉዳተኝነት በአፍሪካ በአፍሪካ ከ80 ሚሊዮን በላይ ሰዎች የተለያየ አይነት የአካል ጉዳት እንዳለባቸው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መረጃ ያሳያል። በአህጉሪቱ በተለይም በየጊዜው የሚከሰቱ አለመረጋጋቶች፣ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች በርካቶችን ለአካልና ለአዕምሮ ጤና ጉዳት የሚዳርጉ ምክንያቶች ሆነው ይጠቀሳሉ። የአብዛኞቹ የአፍሪካ አገራት ፈተናዎች የሆኑት የምጣኔ ሀብት እና የመሠረተ ልማት ችግሮች አካል ጉዳተኞችን የበለጠ ጫና ውስጥ የሚከቱ ከመሆናቸው ባሻገር ተገቢውን ድጋፍ እንዳያገኙ ተግዳሮት ሆነው ቆይተዋል። አካል ጉዳተኝነት በኢትዮጵያ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት የዓለም ጤና ድርጅትና የዓለም ባንክ በኢትዮጵያ 20 ሚሊዮን ዜጎች ከተለያየ ዓይነት የአካል ጉዳት ጋር እንደሚኖሩ ግምት አስቀምጠዋል። ይሁንና የሕዝብና ቤቶች ቆጠራ ከተካሄደ በርካታ ዓመታትን ያስቆጠረ በመሆኑ በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ምን ያህል አካል ጉዳተኞች እንዳሉ ትክክለኛ መረጃ ማግኘትን አዳጋች አድርጎታል። እነዚህ ዜጎች በጎጂ ልማዶችና በተዛባ አመለካከት እንዲሁም በሕግጋት እና በአፈጻጸማቸው ክፍተት ሳቢያ ዘርፈ ብዙ ችግሮችን እየተጋፈጡ እንደሆነም ይጠቁማሉ። በኢትዮጵያ ለአካል ጉዳተኞች የሚመጥን የመሠረተ ልማት አውታር ግንባታ አለመኖርና የአገልግሎት አሰጣጥ ጉድለት በርካቶችን ለከፍተኛ እንግልትና ለተጨማሪ የጤና እክል እንዲጋለጡ አድርጓቸዋል። በመንገዶች ላይ የቁም እና የወለል ምልክቶች አለመኖር፤ በሕንፃዎች ላይ አካል ጉዳተኞችን የሚደግፉ መወጣጫዎች እጥረት፤ የመጸዳጃ እና ሌሎችም ተያያዥ አገልግሎቶች ላይ አካል ጉዳተኞች ተደጋጋሚ ቅሬታ እንዲያነሱም አድርጓል። ኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ የአካል ጉዳተኞች ስምምነትን (Convention) ተቀብላ የሕጓ አካል አድርጋለች። የአካል ጉዳተኞች የሥራ ሥምሪት እና የሕንፃ አዋጆች ጸድቀው ወደ ስራ ተገብቷል። ከ60 በመቶ በላይ አካል ጉዳተኞችን ለቀጠረ ድርጅት ከታክስ እና ከቀረጥ ነፃ የሚያደርግ መመሪያ ወጥቶ ስራ ላይ ውሏል። ይሁን እንጂ አካል ጉዳተኞችን እኩል ተሳታፊና ፍትሃዊ ተጠቃሚ ያደርጋሉ ተብለው የወጡ አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎች መሬት ላይ ወርደው በተጨባጭ ምን ለውጥ አመጡ? አፈፃፀማቸውስ? የሚለው አሁንም ድረስ የበርካቶች ጥያቄ ነው። በኢፌዴሪ ሕገ መንግሥት አንቀፅ 41 ንዑስ አንቀፅ 5 እንደተደነገገው “መንግሥት የአካልና የአዕምሮ ጉዳተኞችን፣ አረጋዊያንና ያለ ወላጅ ወይም ያለ አሳዳጊ የቀሩ ሕፃናትን ለማቋቋምና ለመርዳት የአገሪቱ የኢኮኖሚ አቅም በፈቀደው ደረጃ እንክብካቤ ያደርጋል” የሚል ድንጋጌ ተቀምጧል። መንግሥት አካል ጉዳተኞችን በሚችለው አቅም መርዳት እንዳለበት የሚገልጸው ይህ ድንጋጌ በራሱ ትችት የሚቀርብበት ነው። ድንጋጌው አካል ጉዳተኞች አምራች እንዳልሆኑ እንዲሰማቸው የሚያደርግ መሆኑን ከሚተቹት መካከል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የልዩ ፍላጎትና የአካቶ ትምህርት ክፍል ተባባሪ ፕሮፌሰር ዓለማየሁ ተክለማርያም (ዶ/ር) አንዱ ናቸው። እንደ እርሳቸው፤ በዚህ አንቀፅ አካል ጉዳተኞችን ዕድሜያቸው ካልደረሱ ሕፃናት እንዲሁም ስራ ሰርተው ከጨረሱ አረጋዊያን እኩል ቦታ መስጠቱ ተገቢ አይደለም። አካል ጉዳተኞች በውክልና ካልሆነ ንብረታቸውን ማውረስ እንደማይችሉ በሕገ መንግሥቱ መደንገጉ አካል ጉዳተኞች “አልችልም” የሚል የበታችነት ስሜት እንዲሰማቸው የሚያደርግ ነው። አካል ጉዳተኞች ሁኔታዎች ከተመቻቹላቸውና ዕድሉ ከተሰጣቸው ለራሳቸውም ሆነ ለሀገራቸው ያላቸው አበርክቶ ከፍተኛ ነው። ስለሆነም ይህ ለትርጉም ተጋላጭ የሆነውን አንቀፅ ማስተካከልና የኅብረተሰቡን አመለካከት መቀየር ካልተቻለ አካል ጉዳተኞች በሀገራዊ ጉዳዮች እኩል ተሳታፊና ተጠቃሚ የመሆን ዕድላቸው የሚፈለገውን ያህል አይሆንም። የአካል ጉዳት ያለባቸውን ዜጎች የተመለከቱ ሕጎች ተፈጻሚ እንዳይሆኑ የሚያደርጉ አመራሮችና ፈጻሚዎችን ተጠያቂ ማድረግ ተገቢ ስለመሆኑ የሚጠቁሙት ተባባሪ ፕሮፌሰሩ፤ ሕጉን አስገዳጅ ማድረግ እስካልተቻለ ድረስ ክፍተቱ ሊፈታ አይችልም። ትምህርት ሚኒስቴር የሚያወጣቸው ፖሊሲና ስትራቴጂዎች አካቶ ትምህርትን የሚደግፉ ቢሆኑም፤ በየትምህርት ቤቶቹ ያለው አተገባበር ላይ ክፍተት መኖሩን አመልክተው፤ ይህም ከአመራር አካላት በጎ ፈቃደኝነትና ግንዛቤ ጋር ተያይዞ የሚፈጠር ነው ይላሉ። በኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞችን በተመለከተ ቀደም ካሉት ዓመታት ከነበረው የተሻለ ግንዛቤ ቢፈጠርም፤ አሁንም 90 በመቶ የሚሆኑት ከትምህርት ውጭ ከመሆናቸውም ባለፈ አንዳንድ የሚወጡ ሕጎች አካል ጉዳተኞችን የዘነጉ ናቸው። አካል ጉዳተኞች የትምህርት ዕድል ማግኘታቸው በኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ላይ ተሳታፊ እንዲሆኑ ያደርጋል። ይህም ካላቸው ከፍተኛ ቁጥር አኳያ ለአጠቃላይ ሀገራዊ ምርት ዕድገትና ለድህነት ቅነሳ የድርሻቸውን እንዲወጡ ያስችላል ሲሉም ያክላሉ። በአዲሱ የትምህርት ፍኖተ ካርታ የሁሉም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የዲግሪ ተማሪዎች የአካቶ ትምህርትን እንዲወስዱ መደረጉ አበረታች ውጤት መሆኑን የሚጠቅሱት ተባባሪ ፕሮፌሰሩ፤ “መሰል አስገዳጅ ሁኔታዎች የተዛባ አመለካከትን በዘላቂነት ለመፍታት ያስችላሉ” ይላሉ። በሕገ-መንግሥቱ አንቀፅ 9/4/ ኢትዮጵያ ያፀደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች የሀገሪቷ ሕግ አካል እንዲሆኑ ይደነግጋል። ኢትዮጵያ ካፀደቀቻቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች (Conventions) ውስጥ አንዱ ዓለም-አቀፍ የአካል ጉዳተኞች መብት ስምምነት ሲሆን፤ በዚህ የሕገ መንግሥት ድንጋጌ መሰረት ኮንቬንሽኑ የአገሪቷ የሕግ አካል ሆኗል ማለት ነው። በተጨማሪም የሕገ-መንግሥቱ አንቀፅ 25 ስለእኩልነት መብት ሲዘረዝር ሁሉም ሰዎች በዘር፣ በብሔር፣ በቀለም፣ በፆታ፣ በቋንቋ፣ በሃይማኖት፣ በፖለቲካ፣ በማኅበራዊ አመጣጥ፣ በሃብት፣ በትውልድ ወይም በሌላ አቋም ምክንያት ልዩነት ሳይደረግባቸው እኩልና ተጨባጭ የሕግ ዋስትና የማግኘት መብት እንዳላቸው ይደነግጋል። በዚህ አንቀፅ በአካል ጉዳት ምክንያት ልዩነት መደረግ እንደሌለበት በግልፅ ባያስቀምጥም "በሌላ አቋም ምክንያት" የሚለው ሐረግ አካል ጉዳትንም እንደሚጨምር ታሳቢ ይደረጋል ማለት ነው። በሕገ-መንግሥቱ አንቀፅ 41 ንዑስ አንቀፅ 5 ስለአካል ጉዳተኞች መብት በግልፅ ያስቀመጠ ሲሆን፤ አንቀፁ “መንግሥት የአካልና የአዕምሮ ጉዳተኞችን ለማቋቋምና ለመርዳት የአገሪቷ ኢኮኖሚ በሚፈቅደው መጠን እንክብካቤ ያደርጋል” ይላል። ይህ አንቀፅ አካል ጉዳተኞች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነታቸው እንዲረጋገጥ የሰጠው መብት ቢኖርም ወደ መሬት ወርዶ ተጨባጭ ለውጥ ከማምጣት አኳያ በርካታ ቀሪ ስራዎች አሉ። ሀገሪቷ ከምትከተለው እኩል የሥራ ዕድል መርሆ ጋር የሚጣጣም፣ ለአካል ጉዳተኞች ምቹ የሥራ ሁኔታ የሚፈጥርና በሥራ ሥምሪት የሚደርስባቸውን አድልዎ በፍርድ መድረኮች በቀላሉ ለማስረዳት የሚያስችል አሠራር መዘርጋት ወሳኝ በመሆኑ ስለ አካል ጉዳተኞች የስራ ስምሪት መብት የሚደነግግ የአካል ጉዳተኞች የሥራ ሥምሪት መብት አዋጅ ቁጥር 568/2000 ወጥቶ ተግባራዊ ሆኗል። በዚህ አዋጅ ላይ እንደተመላከተው፤ የሥራው ጠባይ የማይፈቅድ ካልሆነ በቀር የተፈላጊ ችሎታ መመዘኛዎችን አሟልቶ የተገኘና በውድድር ውጤቱ ብልጫ ነጥብ ያገኘ ማንኛውም የአካል ጉዳተኛ በምንም ዓይነት መልኩ መድልዎ ሳይደረግበት፣ በማንኛውም መሥሪያ ቤት ወይም ድርጅት ውስጥ የሚገኝን ክፍት የሥራ ቦታ በቅጥር፣ በዕድገት፣ በድልድል ወይም በዝውውር የመያዝ መብት አለው። በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ አገር በሚሰጥ የሥልጠና ፕሮግራም የመሳተፍ መብት እንዳለውና የተፈላጊ ችሎታ መመዘኛዎችን አሟልቶ የተገኘና ለውድድር ውጤት እኩል ወይም ተቀራራቢ ነጥብ ያገኘ ማንኛውም አካል ጉዳተኛ በምንም ዓይነት መልኩ መድልዎ ሳይደረግበት የተመደበበት የሥራ መደብ የሚያስገኘውን ደመወዝና ሌሎች ጥቅሞች የማግኘት መብት እንዳለው አዋጁ ያትታል። የአካል ጉዳተኞች መብቶች ኮንቬንሽን ስምምነት አዋጅ ቁጥር 676/2002 ላይ እንደተመላከተው፣ የስምምነቱ ዋነኛ ዓላማ ሁሉም አካል ጉዳተኞች በሁሉም ዓይነት ሠብዓዊ መብቶችና መሠረታዊ ነፃነቶች ረገድ ሙሉ እና እኩል ተጠቃሚነት ያላቸው ስለመሆኑ ማረጋገጥ፣ ማሳደግና ለነዚሁ ጥበቃ ማድረግ፣ ብሎም ተፈጥሯዊ ክብራቸውን ከፍ ማድረግ ነው። በዚሁ አዋጅ ስለ ሥራ እና ቅጥር በተቀመጠው አንቀፅ 27 ንዑስ አንቀፅ (ሀ) ላይ ምልመላን፣ ጊዜያዊም ሆነ ቋሚ ቅጥርን፣ በቋሚ ስራ ላይ መቀጠልን፣ የሙያ ዕድገትን፣ ደህንነቱ የተጠበቀና ጤናማ የሥራ ሁኔታዎችን ጨምሮ ተያያዥነት ያላቸውን ጉዳዮች ሁሉ አስመልክቶ በአካል ጉዳት ላይ የተመሰረተ ማናቸውም አይነት አድልዎ እንዳይፈፀም ይከለክላል። የዚሁ አንቀፅ ንዑስ አንቀፅ (ለ) ደግሞ ከወከባ መጠበቅንና ለቅሬታዎች የመፍትሄ ምላሽ ማግኘትን ጨምሮ እኩል ዋጋ ላለው ሥራ እኩል ዕድሎችንም ሆነ እኩል ክፍያ የማግኘት፣ ደህንነታቸው የተጠበቀና ጤናማ የሥራ ሁኔታዎችን ጨምሮ ከሌሎች ጋር በእኩል ደረጃ ለአካል ጉዳተኞች ትክክለኛና ምቹ የሥራ ሁኔታ የማግኘት መብት መስጠቱን ያትታል። ዓለም አቀፉ የሠራተኞች ድርጅት (አይ.ኤል.ኦ) እ.ኤ.አ በ2021 ይፋ ያደረገው መረጃ እንደሚያሳየው በዓለማችን ዕድሜያቸው ለሥራ ከደረሰ ዜጎች 386 ሚሊዮን የሚገመቱት የአካል ጉዳት አለባቸው። በአንዳንድ ታዳጊ አገራትም የአካል ጉዳተኞች ሥራ አጥነት እስከ 80 በመቶ ይደርሳል። ይህም የሚያሳየው አሰሪዎች አካል ጉዳተኞችን የመቅጠር ፍላጎት እንደሌላቸውና ‘አካል ጉዳተኞች መስራት አይችሉም’ የሚል የተሳሳተ ግንዛቤ መያዛቸውን ነው። አካል ጉዳተኝነት ያልበገራቸው ብርቱዎች በጽሁፉ መግቢያ የተዋወቅናቸው የ76 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ አቶ አለበል ሞላ ገና የ13 ዓመት ታዳጊ እያሉ በደረሰባቸው የተሽከርካሪ አደጋ ሁለት እግሮቻቸውን አጥተዋል። አቶ አለበል አዲስ አበባ ተወልደው ማደጋቸው በተሽከርካሪ ወንበር (ዊልቼር) ድጋፍ ወደ ትምህርት ቤትም ሆነ ወደ ስራ ተመላልሰው ለመማርና ለመስራት የሰጣቸው ዕድል ቢኖርም የከተማዋ የእግረኛም ሆኑ የአስፓልት መንገዶች አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ያላደረጉ፤ ለዊልቼር መንቀሳቀሻ በቂ ቦታ የሌላቸው መሆናቸው እንቅስቃሴያቻውን በእጅጉ አክብዶባቸዋል። ከመኖሪያቸው ወደ ትምህርት ቤትና ወደ ስራ ቦታቸው በዊልቼር በሚመላለሱበት ጊዜ በመንገዱ ወጣገባነት ይገጥማቸው የነበረውን ፈተና እና ያሳለፉት ስቃይ እጅግ ከባድ እንደነበር ያስታውሳሉ። ይሁንና አቶ አለበል በርካታ ውጣ ውረዶችና ተግዳሮቶችን አልፈው ትምህርታቸውን በመከታተል ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በማኔጅመንት የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን መያዝ ችለዋል። በመንግሥት መሥሪያ ቤት ተቀጥረው ለ25 ዓመታት አገልግለዋል። ሥራ ለመቀጠር አጋጥሟቸው የነበረውን እልህ አስጨራሽ ትግል አሁንም ድረስ በቁጭት ነው የሚያስታውሱት። ያንን ጊዜ “አስከፊና ተስፋ አስቆራጭ” ሲሉ ይገልፁታል። በፌዴራል መንግሥት ሠራተኞች አዋጅ ቁጥር 1064/2010 ለአካል ጉዳተኞች የሚጠበቁ የሥራ ሁኔታዎችን በተመለከተ እንደተቀመጠው አካል ጉዳተኞች በቅጥር፣ በደረጃ ዕድገት፣ በዝውውር፣ በድልድል፣ በትምህርትና ሥልጠና አፈጻጸም የተጨማሪ ድጋፍ እርምጃ ተጠቃሚ መሆን አለባቸው። ማንኛውም የመንግሥት መስሪያ ቤት የሥራ አካባቢው ለአካል ጉዳተኛ ሠራተኞቹ ምቹ መሆኑን ማረጋገጥ፣ ለሥራ የሚያስፈልጉ መሣሪያዎችንና ቁሳቁሶችን ማሟላትና ስለአጠቃቀማቸው አስፈላጊውን ሥልጠና እንዲያገኙ ማድረግ አለበት። በሌላ በኩል ማንኛውም የመንግሥት መስሪያ ቤት ረዳት ለሚያስፈልገው የአካል ጉዳተኛ የመንግሥት ሠራተኛ ተገቢውን ድጋፍ የሚሰጥ ረዳት እንዲመደብለት የማድረግ ኃላፊነት የተጣለበት ሲሆን፤ በሌሎች ሕጎች ለአካል ጉዳተኞች የተሰጡ መብቶች ለዚህ አዋጅ አፈጻጻም ተግባራዊ እንደሚሆኑ ያስቀምጣል። ይሁን እንጂ ለአቶ አለበል ይህ የመንግሥት ሠራተኞች አዋጅ በወረቀት ላይ ብቻ የሰፈረ የህልም እንጀራ ነው። “ስራ ለመቀጠር ማስታወቂያ በወጣባቸው የመንግሥትና የግል ተቋማት አካል ጉዳት ከሌለባቸው ጋር ተወዳድሮ ማለፍ ትልቅ ፈተና ነበር፤ ፈተናውን በጥሩ ነጥብ አልፌ እንኳን ለቃለ-መጠይቅ ዊልቸሬን እየገፋሁኝ ስገባ ከጠያቂዎቹ ፊት ላይ ያለውን ስሜት በመረዳት ነበር ስራውን እንደማላገኝ እርግጠኛ የምሆነው’’ይላሉ። የዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን አጠናቀው ከተመረቁ ከአራት ዓመታት በኋላ በአንድ የመንግሥት ተቋም ውስጥ በጀማሪ ባለሙያነት የመቀጠር ዕድል ማግኘታቸውንና ይህን ዕድል በመጠቀም አካል ጉዳተኝነት ምንም አይነት ስራ ከመስራት ወደኋላ እንደማያስቀር ለማሳየት ጥረት ሲያደርጉ መቆየታቸውን ይናገራሉ። ይሁንና እንደ ትናንቱ ሁሉ ዛሬም ሆነ ነገ ሁሉም አካል ጉዳተኞችን የሚመለከትበትን መነፅር መጥረግ እንዳለበት አጽንኦት የሚሰጡት አቶ አለበል በተለይም እውቀትና ችሎታው ኖሯቸው እኩል ዕድል ባለማግኘታቸው በከፋ ችግር ውስጥ የሚገኙ አካል ጉዳተኞችን ለመታደግ እያንዳንዱ ዜጋ በሰብዓዊነት ስሜት ሊንቀሳቀስ፣ መንግሥትም ለጉዳዩ ተገቢውን ትኩረት ሊሰጥ እንደሚገባ ያስገነዝባሉ። አቶ አለበል ያለፉበትን የሕይወት ውጣ ውረድ መንገድ ዛሬም በርካታ አካል ጉዳተኞች ይመላለሱበታል። የ12ኛ ክፍል ተማሪዋ ዓይናለም መክብብ ከእነዚህ መካከል አንዷ ነች። ዓይናለም ስትወለድ ጀምሮ ዓይነስውር ናት። ዩኒቨርሲቲ ገብታ ሕግ የመማር ከፍተኛ ፍላጎት ያላት ዓይናለም ለምን ሕግ ማጥናት እንደፈለገች ስትጠየቅ “በሀገራችን ዓይነስውራንን ጨምሮ የተለያየ የአካል ጉዳት ያለባቸው ዜጎች አካል ጉዳት ከሌለባቸው እኩል የትኛውንም አገልግሎት የማግኘት መብታቸው በአግባቡ ተከብሮ ከፍተኛ በሚባሉ የሥራ ቦታዎች ላይ በኃላፊነት እንዲመጡ ካለኝ ፅኑ ፍላጎት ነው” ትላለች። ዓይናለም የምትማርበት ትምህርት ቤት ከብሬል አቅርቦት ጀምሮ የተለያዩ ችግሮች ያሉበት ቢሆንም፤ እርሷ ግን በትምህርቷ ከዓይናማዎች እኩል፤ አንዳንዴም ከእነርሱም በላይ የላቀ ውጤት እያስመዘገበች ትገኛለች። ለዚህ ስኬቷም “እችላለሁ’’ የሚል ጠንካራ ሥነ-ልቦና እንዲኖራት ወላጆቿ ያሳደሩባትን አዎንታዊ ተጽዕኖ በምክንያትነት ትጠቅሳለች። በኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞችን በተመለከተ የሚወጡ ሕጎች በትክክል አይፈፀሙም የሚለውን ቅሬታ ዓይናለምም ትጋራዋለች። ለምን አይፈፀሙም የሚል ጥያቄ ሲነሳም “ሰሚ ጆሮ እና ተመልካች ዓይን” የለም ነው ምላሿ። አካል ጉዳተኞች በከፍተኛ የሥራ ኃላፊነት ላይ ሆነው አገራቸውን እና ሕዝባቸውን እንዲያገለግሉ የሚያግዝ አረንጓዴ መብራት አይታይም። “በፈተና ውስጥም ቢሆን፤ በዩኒቨርሲቲ ቆይታዬ ሕግ አጥንቼ በጥሩ ውጤት እንደምመረቅና ያሰብኩትን እንደማሳካ እርግጠኛ ነኝ” የምትለው ዓይናለም፤ እንደ አገር ለአካል ጉዳተኞች ያለውን ሁለንተናዊ አመለካከት ማስተካከል በተለይም የሕግ ተፈጻሚነትን ማሻሻል የቅድሚያ ቅድሚያ የስራ ትልሟ ስለመሆኑ ትገልፃለች። የሕጎች የተፈጻሚነት ክፍተት በኢትዮጵያ ለአካል ጉዳተኞች ያለው አመለካከት የተንሸዋረረ ነው በሚል የሚነሳውን ቅሬታ የኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማኅበራት ፌዴሬሽን ዋና ዳይሬክተር አቶ ዓባይነህ ጉጆም ይስማሙበታል። በአገሪቷ አካል ጉዳተኞችን አስመልክቶ የሚወጡ ሕጎች በትክክል አካል ጉዳተኞችን እየደገፉ ካለመሆኑ ባሻገር አካል ጉዳተኞችን ብቻ አስመልክቶ የወጣ የሕግ ማዕቀፍ አለመኖሩንም አጥብቀው ይተቻሉ። አካል ጉዳተኞች ለሚያነሷቸው መሰረታዊ ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ የሚሰጥ አሰራር መዘርጋት የግድ ስለመሆኑ አፅንኦት የሚሰጡት አቶ ዓባይነህ “አካል ጉዳተኞችን በተመለከተ የሚወጡ ሕጎችና አሰራሮች በ’እኔ አውቅልሃለሁ’ እሳቤ የወጡና አካል ጉዳተኛውን የማይወክሉ ናቸው” ይላሉ። በአጠቃላይ በሀገሪቷ አካል ጉዳተኞችን አስመልክተው የሚወጡ ሕጎች ተፈጻሚነታቸው ዝቅተኛ ነው። ለዚህ ደግሞ ዋነኛው ምክንያት በአካል ጉዳተኛው ቦታ ሆኖ ችግሩን አለመረዳትና የተቆርቋሪነት ስሜት አለመኖሩ ነው ሲሉም ያክላሉ። በኢትዮጵያ ሕንፃ አዋጅ ቁጥር 624/2001 በሀገሪቷ የሚገነቡ ሕንፃዎች ማሟላት ስለሚገባቸው አጠቃላይ ግዴታዎች ያስቀመጠ ሲሆን፤ በአንቀፅ 36 ስር የሚገነቡ ሕንፃዎች ለአካል ጉዳተኞች ተደራሽ ሊሆኑ እንደሚገባ አስፍሯል። የሕንፃ አዋጁ ይውጣ እንጂ አብዛኞቹ የሚገነቡ ሕንፃዎች አካል ጉዳተኞችን ያላማከሉ ናቸው። ሕጉ አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ እንዲያደርጉ የማያስገድድ በመሆኑ ሕንፃ ገንቢዎቹ ስለአካል ጉዳተኞች መብት ግድ እንዳይሰጣቸው አድርጓል። መንግሥት አካል ጉዳተኞችን በሀገሪቷ ሁለንተናዊ እንቅስቃሴዎች ተሳታፊ ለማድረግ ጉዳታቸውን ታሳቢ ያደረገ ምቹ ሁኔታ መፍጠር እንዳለበት በአፅንኦት የሚገልጹት አቶ ዓባይነህ ፌዴሬሽኑ አካል ጉዳተኞች በሀገሪቷ ሁለንተናዊ ልማት ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ፣ ወጥነት ያለው የአካል ጉዳተኞች ሕግ እንዲወጣ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር ጥረት እያደረገ ስለመሆኑ ነው ያስረዱት። በኢትዮጵያ የሚገነቡ ሕንፃዎችና መንገዶች ከዲዛይን ጀምሮ አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ያደረጉ እንዲሆኑ ማኅበሩ ከኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ባለሥልጣን እና ከአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ጋር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርሟል። የዚህ ስምምነት ዋና ዓላማ አዳዲስ የሚገነቡ መንገዶችና ሕንፃዎች አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ እንዲያደርጉ እንዲሁም ነባር ሕንፃዎችንም ለአካል ጉዳተኞች ምቹ የማድረግ ሁኔታን መፍጠር ነው። አካል ጉዳተኞች በሀገሪቷ ሁለንተናዊ ልማት ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ ሁሉንም ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎ እንደሚያሳድግ የሚገልጹት ዋና ዳይሬክተሩ ለአብነትም ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ስራ ውጤታማነት አካል ጉዳተኞች የድርሻቸውን መወጣት እንዲችሉ በንቃት የሚሳተፉበትን ዕድል ማመቻቸት እንደሚገባም ጠቁመዋል። የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ እያሱ ሰለሞን በመዲናዋ ለዓይነስውራን እና ዊልቼር ለሚጠቀሙ አካል ጉዳተኞች ታስበው የተገነቡ የእግረኛ መንገዶች መኖራቸውን ይናገራሉ። ይሁንና ሁሉም ቦታ ላይ ያሉ መንገዶች የተገነቡት አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ተደርገው ነው ማለት ግን አይቻልም። ይህን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ከኢትዮጵያ አካል ጉዳተኞች ማኅበራት ፌዴሬሽን ጋር በጋራ እየተሰራ ነው ይላሉ። ለአካል ጉዳተኞች ምቹ አካባቢ መፍጠር የሁሉም ባለድርሻ አካላት ግዴታ ስለመሆኑ ያነሱት አቶ እያሱ በተለይ የእግረኛን ጨምሮ የመንገድ መሰረተ ልማቶች አካል ጉዳተኞችን ታሳቢ ያደረጉ እንዲሆኑ የተጀመሩ ጥረቶች ተጠናክረው ሊቀጥሉ ይገባል ሲሉም በአፅንኦት ይገልፃሉ። ቀደም ባለው ጊዜ በተቋማቸው የአካል ጉዳተኞች ጉዳይ ከሌሎች የሥራ ዘርፎች ጋር ተቀናጅቶ ይሰራ እንደነበር በማስታወስ ይህም ጉዳዩ በቂ ትኩረት እንዳያገኝ ከማድረግ ባለፈ አካል ጉዳተኞችን አስመልክቶ የሚሰሩ ስራዎች ውጤታማ እንዳይሆኑ አድርጓል የሚሉት ደግሞ በሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የአካል ጉዳተኞች ግንዛቤ ማስጨበጥ ዴስክ ኃላፊ አቶ ሲሳይ ብርሃኑ ናቸው። አቶ ሲሳይ አክለውም ካለፉት አራት ዓመታት ወዲህ የአካል ጉዳተኞችን ጉዳይ ብቻ የሚከታተል የሥራ ክፍል ተቋቁሞ ወደ ተግባር መግባቱን እና በዚህም ለውጦች መምጣታቸውን ይገልጻሉ። ቀደም ባሉት ዓመታት ስለ አካል ጉዳተኞች የነበረው የተዛባ አመለካከት አሁን አሁን የተወሰኑ መሻሻሎችን ቢያሳይም፤ በርካታ ቀሪ ስራዎች መኖራቸውን አልሸሸጉም። አካል ጉዳተኞችን አስመልክቶ የሚወጡ ሕጎች ተፈጻሚነት ላይ ጉልህ ክፍተቶች አሉ በሚለው አስተያየት አቶ ሲሳይ ይስማማሉ። በተለይ ኢትዮጵያ የአካል ጉዳተኞች መብት ኮንቬንሽንን ተቀብላ ያጸደቀች ቢሆንም፤ ወደ ተግባር ከመቀየር አኳያ በርካታ ክፍተቶች ይስተዋላሉ። እንደ አቶ ሲሳይ ገለፃ እያንዳንዱ የመንግሥት ተቋም አካል ጉዳተኞችን አካቶ መስራት እንዳለበት በኮንቬንሽኑ ተቀምጧል። ይሁንና በየተቋማቱ ከአመራር እስከ ባለሙያ ድረስ አካል ጉዳተኞችን ተደራሽ ሊያደርግ የሚችል አገልግሎት ከመስጠት አኳያ ገና ብዙ ቀሪ ስራዎች አሉ። ለአካል ጉዳተኞች አገልግሎት ከመስጠት አኳያ በርካታ ተቋማት ተደራሽ አይደሉም። በዊልቼር ለሚንቀሳቀሱ፣ ለዓይነስውራን እና መስማት ለተሳናቸው ዜጎች የተቋማት አገልግሎት ተደራሽነት ላይ ብዙ ሊሰራ ይገባልም ይላሉ። ጭላንጭሉ ተስፋ… አካል ጉዳተኞችን በተመለከተ በአንዳንድ ሕጎች ላይ ቀደም ሲል ይስተዋሉ የነበሩ ድክመቶችን የማረም ጥረት ተጀምራል። ለአብነት በኢትዮጵያ የሚገነቡ ሕንፃዎች ለአካል ጉዳተኞች ተደራሽ አለመሆናቸው ተደጋጋሚ ቅሬታ ሲቀርብበት ቆይቷል። ይህን ችግር ለመፍታት የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር የሕንፃ አዋጁ እንዲሻሻል በጋራ እየሰራ ነው። በማሻሻያ አዋጁ ላይ የአካል ጉዳተኞች ማኅበራት ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርጉና አስፈላጊውን ግብዓት እንዲጨምሩም ተደርጓል። አካል ጉዳተኞች ከቀረጥ ነፃ ተሽከርካሪ ማስገባት የሚያስችላቸው መመሪያ ተግባራዊ እንዲሆን ከገንዘብ ሚኒስቴር ጋር በመሆን የአካል ጉዳተኞችን መረጃ የማደራጀት ሥራ እንዲከናወንና በተሰጣቸው ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ ነው። አካል ጉዳተኞች በፌዴራልና በክልል ደረጃ በጉዳት አይነታቸው ተደራጅተው የእኩል ዕድል ተጠቃሚነታቸውና ተሳትፏቸው እንዲጨምር ድጋፍና ክትትል እየተደረገላቸው ይገኛል። ያም ሆኖ አሁንም አንድ ትልቅ ችግር አለ፤ “በኢትዮጵያ የሕዝብና ቤት ቆጠራ ከተካሄደ ዓመታትን ያስቆጠረ በመሆኑ ምን ያህል አካል ጉዳተኞች እንዳሉ ትክክለኛው መረጃ አይታወቅም” ይላሉ። ይህም አካል ጉዳተኞችን እንደ ጉዳት አይነታቸው ለይቶ ተገቢውን ድጋፍና ክትትል ለማድረግ ከባድ ፈተና ሆኗል። አካል ጉዳተኞችን አስመልክቶ የሚወጡ ሕጎች በአግባቡ ተፈጻሚ እንዲሆኑ የጉዳዩ ባለቤቶች የሆኑት ተቋማት የድርሻቸውን ሊወጡ እንደሚገባ፤ ራሳቸው አካል ጉዳተኞችም ለመብቶቻቸው መከበር ይበልጥ መታገል እንደሚገባቸው አስገንዝበዋል። ይህም ብቻ አይደለም የአካል ጉዳተኞች እኩል ተጠቃሚነት ጉዳይ በአንድ ተቋም ብቻ የሚሰራ ባለመሆኑ የሁሉንም የኅብረተሰብ ክፍል ድጋፍ ይሻል።