ቀጥታ፡

የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከል አገልግሎት በሁሉም ክፍለ ከተሞች ተደራሽ ይሆናል

አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከል አገልግሎት እስከ ሚያዚያ 2018 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ በሁሉም ክፍለ ከተሞች ተደራሽ እንደሚሆን የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡ 

የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከል የተገልጋዮችን እንግልት በማስቀረት ውጤታማነትን እያረጋገጠ ነው 

ከንቲባ አዳነች አቤቤ የ'አዲስ መሶብ' ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት የልደታ ቅርንጫፍን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።


 

ከንቲባ አዳነች አቤቤ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፤ ፈጣን የህዝብ አገልግሎት በዜጎች እና በመንግሥት መካከል ያለውን መተማመን ያጎለብታል፡፡ 

በመሆኑም መንግሥት ዘርፉን ለማዘመንና ይበልጥ ተደራሽ ለማድረግ የተለያዩ ስልቶችን በመንደፍ በርካታ ጥረቶችን እያከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡

ከነዚህ ጥረቶችና ተነሳሽነቶች መካከል የአዲስ መሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት አንዱ መሆኑን አውስተዋል፡፡

በዚህም በርካታ ብልሹ አሰራሮችንና አላስፈላጊ የደንበኛ ምልልሶችን በማስቀረት ስር-ነቀል ለውጥ ማምጣት መቻሉን አመላክተዋል፡፡


 

ከዚህ ቀደም ተገንብተው አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኙ የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከላት የህዝቦችን የጊዜ እና የገንዘብ ብክነት ትርጉም ባለው መልኩ እንዳስቀሩ ተናግረዋል፡፡ 

ከዚህ በፊት በተገነቡ የ'አዲስ መሶብ' ዲጂታል የአንድ ማዕከላት ከ120 ሺህ በላይ ዜጎችን ተደራሽ ማድረግ እንደተቻለ አመላክተዋል፡፡

እነዚህ ደንበኞች በሰጡት አስተያየት መሰረት የደንበኞች እርካታ 98 በመቶ መድረስ መቻሉ ተረጋግጧል ነው ያሉት፡፡

በተያዘው ወር ብቻ ተጨማሪ ሶስት የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከላት ለመገንባት ታስቦ ወደ ተግባር መገባቱን ያመላከቱት ከንቲባዋ፤  እስከ ሚያዚያ ወር መጨረሻ ድረስም የከተማዋ ሁሉም ክፍለ ከተሞች በአዲስ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽ እንደሚሆኑ ገልጸዋል፡፡


 

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአዲስ አበባ ፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጀማሉ ጀምበር (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከል  አገልግሎት የመንግስት አገልግሎቶችን ወደ አንድ አሰባስቧል ብለዋል፡፡

በ18 ተቋማት እና በ107 አገልግሎቶች ስራ የጀመረው የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከል አገልግሎት አሁን ላይ የተቋማትን ቁጥር ወደ 22 እና የአገልግሎቶችን ቁጥር ደግሞ ወደ 140 ከፍ ማድረጉን ገልጸዋል፡፡

በዛሬው ዕለት ለምረቃ የበቃው ማዕከል የክፍለ ከተማችንን አገልግሎት አሰጣጥ እርስ በእርስ የሚያስተሳስር ነው ያሉት ደግሞ የልደታ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈጻሚ ልዕልቲ ግደይ ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም