የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከል የተገልጋዮችን እንግልት በማስቀረት ውጤታማነትን እያረጋገጠ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ - ኢዜአ አማርኛ
የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከል የተገልጋዮችን እንግልት በማስቀረት ውጤታማነትን እያረጋገጠ ነው - ከንቲባ አዳነች አቤቤ
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 15/2018(ኢዜአ)፦ የ'አዲስ መሶብ' የአንድ ማዕከል የተገልጋዮችን እንግልት በማስቀረት የመልካም አስተዳደር ውጤታማነትን እያረጋገጠ መሆኑን የአዲስ አበባ ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ 3ኛውን የ'አዲስ መሶብ' ዲጂታል የአንድ ማዕከል አገልግሎት የልደታ ቅርንጫፍን መርቀው ሥራ አስጀምረዋል።
በዚሁ ወቅት ከንቲባ አዳነች አቤቤ እንደተናገሩት፤ የመንግስትን አገልግሎቶች ጥራትና ውጤታማነት የሚያስጠብቅ አስቻይ ምኅዳር እየተፈጠረ ነው።
በዚህም መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ተደራሽነት የዜጎችን እንግልት በማስቀረት የተገልጋዮችን እርካታ እያሻሻለ ይገኛል ብለዋል።
በመሶብ የአንድ ማዕከል የሚሰጡ አገልግሎቶች ጥራትና ውጤታማነትን በማስጠበቅ ብልሹ አሰራሮችን ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ማስቻሉን ተናግረዋል።
በአገልግሎት አሰጣጡ ላይ የተገኘው ተጨባጭ ውጤት ብልሹ አሰራርን በማስቀረት ለዜጎች የመልካም አስተዳደር ጥያቄ መፍትሔ መስጠቱን ገልጸዋል።
በመዲናዋ የተገነቡ የአዲስ መሶብ ዲጂታል የአንድ ማዕከላት የከተማ አስተዳደሩን አገልግሎት በማፋጠን የተገልጋዮችን እርካታ እያሳደገ እንደሚገኝ አንስተዋል።
በቀጣይም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አገልግሎቶችን ፈጣንና ቀልጣፋ በማድረግ የተገልጋዮችን እርካታ የማሻሻል ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም አረጋግጠዋል።