የሚቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎትን በማዘመን የሚኖረውን ጠቀሜታ ለማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ - ኢዜአ አማርኛ
የሚቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎትን በማዘመን የሚኖረውን ጠቀሜታ ለማጎልበት የሚያስችሉ ስራዎች ተጠናክረው ይቀጥላሉ
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 14/2018 (ኢዜአ)፦የሜቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎትን ዘመናዊና ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪ ለማድረግ የጀመራቸውን ስራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታወቀ።
የተፈጥሮ ሃብት አገልግሎት አቅራቢዎች ለሥነ-ምኅዳር ደኅንነት በይበልጥ ሊተጉ ይገባል
ኢንስቲትዩቱ ዓለም አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ ቀንን በኢትዮጵያ ለ45ኛ ጊዜ "ዛሬን መመልከት ፤ነገን ለመጠበቅ " በሚል መሪ ሀሳብ እያከበረ ይገኛል።
የኢትዮጵያ ሚቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተርና በዓለም አቀፉ የሚቲዎሮሎጂ ድርጅት የአፍሪካ አህጉር ፅህፈት ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ፈጠነ ተሾመ እንደገለጹት፤ የአየር ንብረት ለውጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እድገት ላይ አሉታዊ ተፅእኖ እያሳደረ ያለ ጉዳይ ነው።
በመሆኑም ተፅእኖውን መግታት የሚያስችል የሚቲዎሮሎጂ መረጃ አገልግሎት አሰጣጥን ማጠናከር ዋነኛው ጉዳይ መሆኑን አብራርተዋል።
ኢትዮጵያ እያስመዘገበች ያለውን ፈጣን እድገት ለማስቀጠል የሚቲዎሮሎጂ መረጃ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው፤ ኢኒስቲትዩቱ በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት መስጠት የሚያስችል አቅም መገንባት ላይ በትኩረት እየሰራ ይገኛል ብለዋል።
በተለይም አጋር አካላትን ባሳተፈ መልኩ ተጨማሪ አቅም የሚፈጥሩ መሰረተ ልማቶችን ማስፋፋት፣ዘመኑን የዋጁ ቴክኖሎጂዎችን ጥቅም ላይ ማዋል እና የሰው ሀይል ልማት ዋና ዋናዎቹ ስለመሆናቸው አንስተዋል።
በኢትዮጵያ ለ45ኛ ጊዜ የሚከበረው ዓለም አቀፍ የሚቲዎሮሎጂ ቀን ስራዎችን ይበልጥ ለማጠናከርና ተደራሽነትን ለማስፋት አስቻይ ሁኔታ እንደሚፈጥር አክለዋል።
በተጨማሪም ኢንስቲትዩቱ የሚሰጠውን አገልግሎት በዘመናዊ የሚቲዎሮሎጂ ሳይንስ ላይ በመመስረት ዛሬ የተሻለ መረጃ በመያዝ የተሻለ ነገን ለመገንባት የተለያዩ የጥናትና ምርምር ስራዎችን እየሰራ ስለመሆኑን ገልጸዋል።