ቀጥታ፡

ለኢድ አልፈጥር በዓል በቂ ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እያገኘን ነው- የሰመራ ሎጊያ ከተማ ነዋሪዎች 

ሰመራ፤ መጋቢት 10/2018 (ኢዜአ)፦ ለኢድ አልፈጥር በዓል  በተመጣጣኝ ዋጋ በቂ የምርትና የእርድ እንስሳት አቅርቦት መኖሩን የሰመራ ሎጊያ ከተማ ነዋሪዎች ገለጹ።

በወልቂጤ ከተማ ለኢድ አልፈጥር በዓል ምርቶች በበቂ ሁኔታ ቀርበዋል

የ1447ኛው የኢድ አልፈጥር በዓል በነገው እለት በኢድ ሰላትና በተለያዩ ዝግጅቶች የሚከበር መሆኑ ይታወቃል።

በዓሉ እርድና ሌሎች አስፈላጊ ዝግጅቶችን በማድረግ ዘመድ ጎረቤት በመጠራራት፣ የተቸገሩ ወገኖችን ማእድ በማጋራት በአብሮነት የሚከበር መሆኑ ይታወቃል።

በአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያም ለበዓሉ የእርድ እንስሳት ሲገዙ ያገኘናቸው አቶ አብዱ መሐመድ እና አቶ እስማኤል ዓሊ፤ የእርድ እንስሳት እንዲሁም የግብርና እና ኢንዱስትሪ ምርት በበቂ መጠን መኖሩን ገልጸዋል።


 

የገበያው ዋጋ ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር እምብዛም ያልተራራቀ እና ተቀራራቢ መሆኑን አስታውሰው በተመጣጣኝ ዋጋ በቂ የምርትና የእርድ እንስሳት አቅርቦት መኖሩን ተናግረዋል።

ወይዘሮ ፋጡማ መሐመድ በበኩላቸው፤ ለኢድ አልባሳትም ሆነ ምርቶች በአማራጭ መቅረቡን ገልጸዋል።

በመሆኑም ሸማቹ በፈለገው ጥራትና በተለያዩ የዋጋ አማራጮች እየሸመተ መሆኑን ገልጸው እርሳቸውም የበዓል ልብስ እና የተለያዩ ምርቶችን መግዛታቸውን ተናግረዋል።

በንግድ ስራ ላይ የተሰማሩት አቶ ተስፋዬ ታደሰ፤ የበዓል ገበያ በአቅርቦት ብዙ አማራጭ መኖሩንና የተረጋጋ ዋጋ እንዳለ ገልጸዋል።


 

በዚህም መሰረት ሸማቾች ለበዓል የሚሆናቸውን በተለያዩ ምርቶች  እየገዙ መሆኑን ተናግረዋል። 

የዒድ ዓል ፈጥር በዓል የአብሮነት፣ የምስጋና እና የደስታ ቀን በመሆኑ ህዝበ ሙስሊሙ በጋራ ሰላት ከሰገደ በኋላ በመጠያየቅ እና አብሮነት የሚያከብረው መሆኑ ይታወቃል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም