ቀጥታ፡

በወልቂጤ ከተማ ለኢድ አልፈጥር በዓል ምርቶች በበቂ ሁኔታ ቀርበዋል

ወልቂጤ፤መጋቢት 10/2018 (ኢዜአ)፦ በወልቂጤ ከተማ ገበያ ለኢድ አልፈጥር በዓል የፍጆታ ምርቶችና የእርድ እንስሳት በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውን የከተማው ሸማቾች እና ነጋዴዎች ተናገሩ።

የጎንደር ከተማ አስተዳደር የኢድ አልፈጥር በዓልን ምክንያት በማድረግ ለአቅመ ደካማ ወገኖች ማዕድ አጋራ

በበዓል ገበያ ላይ ሕገወጥ ተግባራትን ለመከላከል ግብረ ኃይል በማቋቋም እየተሠራ መሆኑን የከተማው ንግድና ገበያ ልማት ጽሕፈት ቤት ገልጿል። 

በከተማ አስተዳደሩ በኩል ከዋናው ገበያ ባለፈ በተለያዩ አካባቢዎች አማራጭ ገበያዎች በመመቻቸታቸው ሸማቹ ምርቶችን በቀጥታ እንዲያገኝ ተደርጓል።

በገበያው ሲሸምቱ ያገኘናቸው አቶ አብድረዛቅ መሐመድ፤ ለበዓል ገበያ የእርድ እንስሳትን ጨምሮ ተፈላጊ የፍጆታ ምርቶች በበቂ ሁኔታ መቅረባቸውንና ዋጋውም ተመጣጣኝ መሆኑን ገልጸዋል። 

በዓሉን በአካባቢያቸው ያሉ አቅመ ደካሞችን በማሰብና በመደገፍ በአብሮነት ለማክበር መዘጋጀታቸውንም ተናግረዋል።

አቶ መሐመድ ሙደሲር የተባሉ ሌላው ሸማች በበኩላቸው፤ በበዓል ገበያው ሁሉም ሰው በአቅሙ ገዝቶ ለመጠቀም በሚያስችለው መልኩ ምርቶች መቅረባቸውን ገልጸዋል። 

በተለይ ለግብርና ምርታማነት የተሰጠው ትኩረት በገበያው የተሻለ የምርት አቅርቦትና የተረጋጋ የግብይት ሂደት እንዲኖር ማድረጉን ጠቁመዋል።

በአትክልትና ፍራፍሬ ንግድ ሥራ የተሰማሩት ወይዘሮ ዘይነባ አወል፤ በአውደ ዓመት ገበያው የምርት እጥረትም ሆነ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳልተስተዋለ ተናግረዋል። 

በወልቂጤ ከተማ በበግና ፍየል ሽያጭ ሥራ የሚተዳደረው አቶ አወል ቢራቱ በበኩሉ፤ ለበዓሉ የእርድ እንስሳት አቅርቦት በበቂ ሁኔታ እንዳለና በሸማቹ አቅም ልክ ግብይት መፈጸም እንደሚቻል ገልጿል።

የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ንግድና ገበያ ልማት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጴጥሮስ አስራት በበኩላቸው፤ ለኢድ አልፈጥር በዓል ምርት በበቂ ሁኔታ መቅረቡን ተናግረዋል። 

በዓሉን ታሳቢ በማድረግ ከዋናው ገበያ በተጨማሪ የቅዳሜና እሁድ ገበያዎችና ሌሎች የግብይት ማዕከላትን በማመቻቸት ነዋሪው በአቅራቢያው መሸመት የሚችልበት መንገድ መፈጠሩንም ጠቁመዋል።

በተጨማሪም ስኳር፣ እንቁላል፣ ዘይትና ሽንኩርት በሸማቾች ማኅበራት በኩል ለህብረተሰቡ እንዲደርስ መደረጉን ነው የተናገሩት።

ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ እንዳይኖርና ሕገወጥ ተግባርን ለመከላከል ግብረ ኃይል ተቋቁሞ እየተሠራ መሆኑን የጠቆሙት ኃላፊው፤ ሕብረተሰቡ በግብይት ወቅት አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ እንዳለበትም አሳስበዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም