ቀጥታ፡

በክልሉ የግብርና አቅምን በመለየት የተከናወኑ የአሰራር ማሻሻያዎች ውጤት አምጥተዋል

ዲላ ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና አቅምን በጥናት በመለየት የተከናወኑ የአሰራር ማሻሻያዎች እና በቴክኖሎጂ የተደገፉ ትግበራዎች ውጤት ማምጣታቸውን የክልሉ ግብርና ቢሮ ገለጸ።

በክልሉ የግብርና ምርምር ውጤቶች ለተጠቃሚው በመድረሳቸው በዘርፉ ተጨባጭ ውጤት እየመጣ ነው

የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት "በምርምር የታገዘ ግብርና፣ የበለፀገ ማኅበረሰብ፣ የማይበገር ኢኮኖሚ መገንባት" በሚል መሪ ቃል ያዘጋጀው አውደ ጥናት በዲላ ከተማ እየተካሄደ ይገኛል።


 

በአውደ ጥናቱ በሰብል፣ በእንስሳትና በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ እንዲሁም በተለያዩ ዘርፎች የተሰሩ 1 ሺህ 107 የምርምር ሥራዎች ቀርበው የሚገመገሙ መሆኑ ተመላክቷል።

በወቅቱም በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ግብርና ቢሮ ኃላፊ መሪሁን ፍቅሩ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ በክልሉ የግብርና ሽግግርን ለማፋጠን ጥናትና ምርምርን መሠረት ያደረጉ በርካታ ተግባራት እየተከናወኑ ነው። 

በተለይም የክልሉን የግብርና አቅም በመለየት የተከናወኑ የአሠራር ማሻሻያዎችና በቴክኖሎጂ የተደገፉ ትግበራዎች ውጤት ማምጣታቸውን ጠቁመዋል። 

ለዚህም በክልሉ በሩዝ ልማት የተመዘገበውን ውጤት ለአብነት በመጥቀስ፣ መሰል ውጤታማ የምርምር ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸው አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የሰብል ምርምር ዳይሬክተር ፍቃዱ ግርማ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የግብርና ምርምርን ከሀገራዊ የልማት ኢኒሼቲቮች ጋር በማጣጣም በተከናወኑ ተግባራት ስኬት መገኘቱን ገልጸዋል። 


 

በተለይም በአረንጓዴ አሻራ፣ በበጋ መስኖ ስንዴ ልማት እንዲሁም በሌማት ትሩፋት ኢኒሼቲቮች ግብርናውን ለማሻገር የሚያስችሉ ተጨማሪ አቅሞችን መፍጠር መቻሉን ተናግረዋል። 

ግብርናው ለተለያዩ የኢኮኖሚ ዘርፎች አጋዥ ኃይል ሆኖ በመውጣት ሽግግሩን እንዲመራም እየተከናወኑ ያሉ የምርምር ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉም ገልጸዋል።

የጌዴኦ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ዝናቡ ወልዴ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ በዞኑ በቡናና በእንሰት ልማት ላይ የታየው ለውጥ በሰብሎቹ ላይ የተካሄዱ የምርምር ሥራዎች ውጤታማ በመሆናቸው የመጣ ነው ብለዋል። 


 

በተለይም በቡና ልማት ረገድ በምርምር ግኝቶች ላይ ተመስርተው የወጡ የተሻሻሉ ዝርያዎች፣ በሄክታር በአማካይ 5 ኩንታል የነበረውን የቡና ምርት ወደ 11 ኩንታል ማሳደጉን አስረድተዋል። 

ይሁን እንጂ የአፈር አሲዳማነት ዛሬም የዞኑ የግብርና ልማት ማነቆ መሆኑን በመጥቀስ፣ በዚህ ረገድ የሚከናወኑ የምርምር ሥራዎች መጠናከር እንዳለባቸው አሳስበዋል።

የአውደ ጥናቱ ዓላማ የተቀናጁ የምርምር ሥራዎችን በማውጣት የተሻለ የግብርና ልማትን ማረጋገጥ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ሥራ አስፈጻሚ አብዮት መብራቴ (ዶ/ር) ናቸው። 


 

ኢንስቲትዩቱ የተለያዩ የግብርና ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ የግብርና ምርታማነትን እያገዘ መሆኑን ገልጸው፤ በተያዘው ዓመት በ470 ሄክታር የአርሶ አደር ማሳ ላይ ሰርቶ በማሳየት የተሻሻሉ ቴክኖሎጂዎችን ከማስተዋወቅ ባለፈ፣ የምርጥ ዘር አቅርቦትን በራስ አቅም ለመሸፈን የሚያስችል አቅም መፈጠሩን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም