በክልሉ የግብርና ምርምር ውጤቶች ለተጠቃሚው በመድረሳቸው በዘርፉ ተጨባጭ ውጤት እየመጣ ነው - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ የግብርና ምርምር ውጤቶች ለተጠቃሚው በመድረሳቸው በዘርፉ ተጨባጭ ውጤት እየመጣ ነው
ሆሳእና፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የግብርና ምርምር ውጤቶች ለተጠቃሚው በመድረሳቸው በዘርፉ ተጨባጭ ለውጦች እየተመዘገቡ መሆኑን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡
የክልሉ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዓመታዊ የምርምር ሥራዎች ግምገማ መድረክ ዛሬ በሆሳዕና ከተማ ተካሂዷል።
በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የግብርናና ገጠር ልማት ክላስተር አስተባበሪና የክልሉ ግብርና ቢሮ ሀላፊ ኡስማን ሱሩር በዚህ ወቅት እንደገለጹት፣ በክልሉ ምርታማነትን የሚያሳድጉ የምርምር ሥራዎች ለተጠቃሚው በመድረሳቸው በግብርናው ዘርፍ ተጨባጭ ለውጥ እየመጣ ነው፡፡
የግብርና ምርምር ተቋማት አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ፣ ከፍተኛ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችን በማላመድና ዘመናዊ የእርሻ አስተዳደር ዘዴዎችን በማስተዋወቅ የዘርፉን ምርታማነት እያሳደጉ ነው ብለዋል፡፡
በተለይም በሽታና ድርቅን ተቋቁመው የተሻለ ምርት የሚሰጡ ዝርያዎችን፣ የቅመማቅመም ምርቶች እንዲሁም አትክልትና ፍራፍሬዎችን ለአርሶ አደሮች የማቅረብ ሥራ በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ግብርናን በማዘመን ኢኮኖሚያዊ መዋቅራዊ ሽግግርን ከግብ ለማድረስ ተመራማሪዎች አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን ማፍለቅ፣ ማባዛትና ማሰራጨት ላይ ተግተው ሊሰሩ እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ፀጋዬ ተረፈ በበኩላቸው የአየር ንብረት ለውጥን ተቋቁመው የተሻለ ምርት በሚሰጡ ዝርያዎች ላይ ምርምር እየተካሄደ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የምርምር ውጤቶች ለአርሶ አደሮች ደርሰው በተጨባጭ ማሳ ላይ እንዲተገበሩ ከዩኒቨርሲቲዎች እና ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር በቅርበት እየሰራን ነው ብለዋል።
በተያዘው በጀት ዓመትም ምርትና ምርታማነትን የሚያሳድጉ የምርምር ውጤቶችን ለአርሶ አድሩና ለተጠቃሚዎች ተደራሽ መደረጋቸውን ገልጸዋል።
ከዛሬ ጀምሮ ለሦስት ቀናት በሚቆየው መድረክ ከተለያዩ ተቋማት የቀረቡ ከ265 በላይ የምርምር ሥራዎች እንደሚገመገሙ ተመላክቷል።