ገዢ ትርክትን በማስረፅ ሀገር ተረካቢ ትውልድ በማፍራት ለዘላቂ ሰላምና ልማት መረጋገጥ የድርሻችንን እንወጣለን- መምህራን - ኢዜአ አማርኛ
ገዢ ትርክትን በማስረፅ ሀገር ተረካቢ ትውልድ በማፍራት ለዘላቂ ሰላምና ልማት መረጋገጥ የድርሻችንን እንወጣለን- መምህራን
ደሴ ፤ መጋቢት 1/2018(ኢዜአ)፦ ገዢ ትርክትን በማስረፅ ሀገር ተረካቢ ትውልድ በማፍራት ለዘላቂ ሰላምና ልማት መረጋገጥ የድርሻችንን እንወጣለን ሲሉ በደሴ ከተማ የሚገኙ መምህራን ገለጹ።
ትውልዱ በሀገር ሰላምና ልማት ውስጥ የሚያደርገውን ተሳትፎ እንዲያጠናክር የድርሻችንን እንወጣለን- የሀይማኖት አባቶች
የደሴ ከተማ አስተዳደር "ለሰላም ዘብ እንቆማለን፣ የልማት አርበኛም እንሆናለን" በሚል መሪ ሀሳብ ከመምህራን ጋር የውይይት መድረክ አካሄዷል።
የውይይቱ ተሳታፊ መምህር ተስፋዬ ከበደ ፤ ሰላም ለሁሉም አስፈላጊ በመሆኑ ከመማር ማስተማር ሥራቸው በተጓዳኝ ለከተማው ዘላቂ ሰላምና ልማት የበኩላችንን ድርሻ እየተወጣን ነው ብለዋል።
መምህራን ለሀገር ተረካቢው ትውልድ ገዢ ትርክትን በማስረፅ ፣ ሰላምና ልማትን ከማረጋገጥ ባሻገር በተለይ እንደ ሀገር የተጀመሩ ሜጋ ፕሮጀክቶች እንዲሳኩ የድርሻችንን እንወጣለን ብለዋል።
መንግስት በአሁኑ ወቅት ሰላምን ለማምጣት የሰጠውን ሰፊ እድል ያደነቁት መምህሩ ትውልዱ የሰላም ኃይል በመሆን ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት መጠናከር እየተደረገ ያለውን ጥረት እንዲደግፍም የበኩላቸውን እንደሚወጡ ነው ያረጋገጡት።
ሌላው የውይይቱ ተሳታፊ መምህር ወንድምነህ ይልማ፤ ሀገር ተረካቢ ትውልድን ከማነጽ ባሻገር ለከተማዋ ሰላምና ልማት የድርሻቸውን ለመወጣት በቁርጠኝነት እየሰሩ መሆኑን ይገልፃሉ።
በተለይ አሰባሳቢ ትርክት ላይ በመመስረት የተማሪዎችንና የህብረተሰቡን ግንዛቤ በማሳደግ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ስር እንዲሰድ የድርሻቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።
''አንድነታችንን ጠብቀን ለከተማችን ብሎም ለሀገራችን ዘላቂ ሰላምና ልማት መረጋገጥ የድርሻችንን እንወጣለን" ያሉት ደግሞ የውይይቱ ተሳታፊ መምህርት አልማዝ አለባቸው ናቸው።
ከፀጥታ አካላት ጋር በመቀናጀት የአካባቢያችንን ሰላም ተደራጅተን በመጠበቅ በከተማዋ የሰፈነውን ሰላም ዘላቂ ለማድረግ የምናደርገውን አስተዋጽኦ እናጠናክራለን ብለዋል።
የደሴ ከተማ አስተዳደር ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ አቶ ሳሙኤል ሞላልኝ በመድረኩ እንደገለፁት፣ ከማሕበረሰቡ ጋር በመቀናጀት ሰላምን ዘላቂ ለማድረግና የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ለማስቀጠል እየተሰራ ነው።
መምህራንም ሀገር ተረካቢ ትውልድን ለመፍጠር ከሚያደርጉት ጥረት ባሻገር ለከተማው ሰላምና ልማት የድርሻቸውን ማበርከት መቻላቸው የሚያስመሰግን ነው ብለዋል።
በቀጣይም የጋራ ትርክትን በመገንባት፣ ለአንድነት፣ ለሰላምና ለልማት የሚያደርጉትን ጥረት አጠናክረው ሊቀጥሉ እንደሚገባ አሳስበዋል።
በመድረኩም የክልል፣ የከተማ አመራሮችና ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል።