ለሎጎ ሐይቅ ሪዞርት መዳረሻነት የሚያገለግል የመሰረተ ልማት ግንባታ እየተፋጠነ - ኢዜአ አማርኛ
ለሎጎ ሐይቅ ሪዞርት መዳረሻነት የሚያገለግል የመሰረተ ልማት ግንባታ እየተፋጠነ
ደሴ፤ የካቲት 30 /2018(ኢዜአ)፦በሐይቅ ከተማ አስተዳደር በሚገኘው የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት እየተከናወነ ያለው የመሰረተ ልማት ግንባታ እየተፋጠነ መሆኑን የከተማ አስተዳደሩ ገለፀ።
በክልሉ የሚገኙ የቱሪዝም መዳረሻዎችን በማልማት ከዘርፉ የሚገኝን ገቢ ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል
የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት በቅርቡ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት መደረጉ በአካባቢው ለቱሪዝም ዘርፉ መነቃቃት እድልን ፈጥሯል።
ሪዞርቱ የአካባቢውን ፀጋ ወደ ኢኮኖሚ ለመቀየር ከማገዙም ባለፈ ሀብቱን በዓለም ለማስተዋወቅ፣ ለዜጎች የሥራ እድል ለመፍጠርና ለከተማው እድገት አዎንታዊ ሚና እንዳለውም እሙን ነው።
በሐይቁ አካባቢ እየተከናወኑ ባሉ የልማት ስራዎች ላይ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባው አቶ ከድር መሀመድ ለኢዜአ እንዳሉት፣ በከተማው በርካታ የቱሪስት መዳረሻ ሥፍራዎች ቢኖሩም ለምተው ጥቅም መስጠት ሳይችሉ ቆይተዋል።
የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት መገንባትን ተከትሎ ለሪዞርቱ መዳረሻነት የሚያገለግል መሰረተ ልማት ግንባታ እየተፋጠነ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ይህም ከተማ አስተዳደሩ በመደበው ከ150 ሚሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ እየተከናወነ መሆኑን ጠቁመው በዚህም የብስክሌት፣ የእግረኛና ሌሎች መዝናኛዎች መካተታቸውን ተናግረዋል።
እንዲሁም በፌዴራል እና በክልል መንግስት በጀት ከሐይቅ ከተማ በፒያሳ አደባባይ አድርጎ እስከ ሎጎ ሐይቅ ሪዞርት የሚወስደው ሁለት ነጥብ አንድ ኪሎ ሜትር አስፋልት መንገድ ግንባታ እየተፋጠነ ይገኛል ብለዋል።
መንገዱ ደረጃውን የጠበቀ በግራና በቀኝ የእግረኛና የብስክሌት መንገድ ጭምር ያለው መሆኑንም አመልክተዋል።
የሐይቅ ከተማ ነዋሪ አቶ አብዱ ሙሄ በበኩላቸው፣ የሎጎ ሐይቅ ሪዞርት በከተማው ያሉ የታሪክ እና የገዳማት መገኛዎችን ለዓለም ያሳየ እና ለዘመናት የልማት ጥያቄዎች መልስ የሰጠ ነው ብለዋል።
ሪዞርቱ የበለጠ የቱሪስት መዳረሻ እና ለጎብኚዎችም ምቹ እንዲሆን የአስፋልት መንገድና ሌሎችም የልማት ስራዎች እየተፋጠኑ መሆኑን ገልፀዋል።
የከተማዋን ሰላም በአንድነት በመጠበቅ ሪዞርቱ የቱሪስት መዳረሻ እንዲሆን እየተከናወኑ ያሉ የልማት ስራዎች እንዲፋጠኑ በገንዘብና በጉልበት እያገዝን እንገኛለን ያለው ደግሞ ወጣት ሰይድ ዑመር ነው።
ሪዞርቱ የተረሳውን የተፈጥሮ ፀጋ ወደ ሚጨበጥ ኢኮኖሚ የሚቀይር የልማት አሻራ በመሆኑ ተደስተናል ብሏል።
የከተማው የኮሪደር ልማት እየተጠናቀቀ በመሆኑ ለሎጎ ሐይቅ ሪዞርት ጎብኚዎች ምቹ ሁኔታን እንደሚፈጥር ነው የገለጸው፡፡