የግብርና አገልግሎቶችን ከዲጂታል መታወቂያ ጋር የማስተሳሰር ተግባር እየተከናወነ ነው - ኢዜአ አማርኛ
የግብርና አገልግሎቶችን ከዲጂታል መታወቂያ ጋር የማስተሳሰር ተግባር እየተከናወነ ነው
ቦንጋ፣ የካቲት 24/2018(ኢዜአ)፦ በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የግብርና አገልግሎቶችን የማዘመንና ከፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ጋር የማስተሳሰር ተግባር እየተከናወነ መሆኑ ተገለጸ።
በደቡብ ኦሞ ዞን የሚገኙ እምቅ ሃብቶችን በሳይንሳዊ ጥናትና ምርምር በማገዝ የህዝቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ መስራት ይገባል
የክልሉ ግብርና ቢሮ ከግብርና ሚኒስቴር ጋር በመተባበር “ዲጂታል ማንነት ለተረጋገጠ ይዞታ ባለቤትነትና ለላቀ የፋይናንስ ተጠቃሚነት!'' በሚል መሪ ሀሳብ ያዘጋጀው የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ የንቅናቄ መድረክ በቦንጋ ከተማ እየተካሄደ ነው።
የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳደርና የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ማስረሻ በላቸው የንቅናቄ መድረኩን ባስጀመሩበት ወቅት እንደገለፁት፤ ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት በሚደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ የፋይዳ መታወቂያን ማዳረስ አንዱ ነው።
በአሁኑ ወቅትም የገጠር ትራንፎርሜሽንን እውን ለማድረግ ፈጣንና ዘመናዊ የግብርና አገልግሎቶችን ለአርሶና አርብቶ አደሩ መስጠት እንዲቻል እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰዋል።ለዚህም የፋይዳ መታወቂያን የማዳረስ ስራ እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
የግብርና አገልግሎቶችን በማዘመን ከፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ጋር ማስተሳሰር የአርሶና አርብቶ አደሩን የብድርና የፋይናንስ ተጠቃሚነት ችግር ለመፍታት እንደሚያስችልም ነው የገለጹት።
ይህም አርሶና አርብቶ አደሩ ባለው እሴት ላይ ተመርኩዞ የፋይናንስ ተጠቃሚ እንዲሆን እንደሚያግዘው ነው የተናገሩት።
የአርሶና አርብቶ አደሩ ዋነኛ ሀብት የሆነውን የመሬት ልኬትን ከሀገራዊ መረጃ ስርዓት ጋር በማቆራኘትና ከዲጂታል መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር የፋይናንስ ተደራሽነትን የማረጋገጥ ተግባር እየተከናወነ መሆኑንም አብራርተዋል።
በክልሉ በከተማና በገጠር ከ682 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎችን የዲጂታል መታወቂያ ባለቤት ለማድረግ መቻሉንም ገልጸዋል።