ቀጥታ፡

የኢትዮጵያን የዲጂታል ኢኮኖሚ ለማሳለጥ ወጣቶችን በቴክኖሎጂ የማብቃት ስራ ትኩረት ተሰጥቶታል

አምቦ፤ የካቲት 20/2018 (ኢዜአ)፡- የኢትዮጵያን የዲጂታል ኢኮኖሚ ለማሳለጥ ወጣቶችን በቴክኖሎጂ ለማብቃት ስራ ትኩረት መሰጠቱን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) አስታወቁ።

የሰውሰራሽ አስተውሎት ትምህርትን ከአንደኛ ደረጃ ጀምሮ መስጠት የሚያስችል ዝግጅት እየተደረገ ነው

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከኦሮሚያ ክልል ሳይንስና ቴክኖሎጂ ቢሮ ጋር በመተባበር በአምቦ ከተማ ያስገነባው የወጣቶች ኢኖቬሽን ኢንኩቤሽን ማዕከል እና የአምቦ ስታርት አፕ ማዕከል ተመርቋል።


 

በምረቃ መርሃ ግብሩ ላይ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፣ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንት አወሉ አብዲ እና ሌሎች የፌዴራል እና የክልል አመራሮች ተገኝተዋል።

በዚሁ ጊዜ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር)፣ ኢትዮጵያ የጀመረችውን የዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ ለማስቀጠል ወጣቶችን በቴክኖሎጂ፣ በሳይንስና በፈጠራ ለማብቃት ስራ ትኩረት ተሰጥቷል ብለዋል።

ዛሬ በአምቦ ከተማ አገልግሎት የጀመረው ማዕከልም በአገር አቀፍ ደረጃ የተጀመረውን የኢኖቬሽን ሥነ-ምህዳር የማጠናከርና የቴክኖሎጂ ክፍተቶችን ለመሙላት ያግዛል ብለዋል።


 

መሰል የኢኖቬሽን ኢንኩቤሽን ማዕከላት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ተገንብተው የዜጎችን ችግር እየፈቱ መሆኑን ጠቅሰው የአምቦው ማዕከልም ወጣቶችን በቴክኖሎጂ በማብቃት የማኅበረሰቡን ችግር የሚፈቱ የፈጠራ ሥራዎች የሚፈልቁበት ይሆናል ነው ያሉት።

የኦሮሚያ ክልል ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አወሉ አብዲ በበኩላቸው፤ የአንድን ሀገር ዕድገት ማፋጠን የሚቻለው በቴክኖሎጂ ማገዝ ሲቻል መሆኑን ገልጸዋል። 


 

የክልሉ መንግሥት ግብርናንና ሌሎች ዘርፎችን በቴክኖሎጂ በማስደገፍ የሕዝቡን ኑሮ ለማሻሻልና የሀገሪቱን የዲጂታል ኢኮኖሚ ግብ ለማሳካት ዘርፈ ብዙ ሥራዎችን እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የአምቦ ከተማ ከንቲባ አቶ ሃጫሉ ገመቹ፤ ማዕከሉ ወጣቶች የሚዝናኑበት ብቻ ሳይሆን፣ ዕውቀታቸውን ወደ ተግባር በመለወጥ ማኅበረሰባቸውን የሚያገለግሉበት የፈጠራ ማዕከል መሆኑን አብራርተዋል።


 

በማዕከሉ የቴክኖሎጂ ሥልጠና የወሰዱ ወጣቶች በበኩላቸው፣ ባገኙት ዕውቀት ተጠቅመው የሀገሪቱን ዕድገት ለማፋጠን መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።


 

በተለይም የድረ-ገጽ ማበልጸግ ሥልጠና በመውሰድ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና ማኅበረሰብን በፈጠራ ለማገዝ መዘጋጀታቸውን ጠቁመዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም