ቀጥታ፡

እያደገ የመጣው የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂ በዜጎች ኑሮ ላይ ተጨባጭ ለውጥ አምጥቷል

ደብረ ማርቆስ ፤ የካቲት 19/2018 (ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን እያደገ የመጣው የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂ ተደራሽነት የዜጎች ኑሮ ላይ ተጨባጭ ለውጥ ማምጣቱ ተገለጸ።

የገጠር መሬትን ከፋይዳ መታወቂያ ጋር በማስተሳሰር አርሶአደሩ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተሰራ ነው

ለኢዜአ አስተያየታቸውን የሰጡ የምስራቅ ጎጃም ዞን አርሶ-አደሮች፤ አማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂዎችን መጠቀማቸው የደን ጭፍጨፋን መቀነስ፣ ጤናቸውን መጠበቅና ምርታማነታቸውን ማሳደግ እንዳስቻላቸው ገልጸዋል።

የጎዛምን ወረዳ ደሳ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ጌታቸው አንሙት፣ የባዮጋዝ ቴክኖሎጂን በመገንባት ለምግብ ማብሰያና ለመብራት አገልግሎት መጠቀም መጀመራቸውን ተናግረዋል። ይህም ቀደም ሲል ለማገዶና ለናፍጣ ሳወጣ የነበረውን ወጪ ቆጥቦልኛል ብለዋል።

አማራጭ የኢነርጂ ቴክኖሎጂው የእርሳቸውንና ቤተሰባቸውን ጤና እንዲጠብቁ ከማድረግ ባለፈ ማገዶ ፍለጋ ጫካ በመሄድ ይደረስባቸው የነበረውን  እንግልት መቀነሱን ገልጸዋል።

አርሶ አደር ጌታሁነኝ ብርሃን በበኩላቸው፣ ከባዮጋዝ የሚገኘውን ተረፈ ምርት እንደ ማዳበሪያ በመጠቀማቸው የአትክልትና ሰብል ምርታማነታቸው መጨመሩን ገልጸዋል።

ቴክኖሎጂውን ለተለያዩ አገለግሎቶች እያዋሉት መሆኑንና በዚህም በኑሯቸው ላይ ተጨባጭ ለውጥ መምጣቱን አንስተዋል።

የእነደድ ወረዳ ነዋሪ ዘውዲቱ ጥላሁን፣ ዘመናዊና ሀይል ቆጣቢ ምድጃዎችን መጠቀም መጀመራቸው ከዚህ ቀደም በእሳት ነበልባልና በጭስ ምክንያት ይደርስባቸው ከነበረው የጤና መታወክ እንደታደጋቸው ገልጸዋል።

የምስራቅ ጎጃም ዞን ውሃና ኢነርጅ መምሪያ ሃላፊ ፍሬው ካሴ እንደገለጹት፤ በዞኑ አማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂ ተደራሽነትን በማስፋት የአርሶአደሩን ኑሮ ለማሻሻል ጥረት እየተደረገ ነው።

በ2018 በጀት ዓመት ከ44ሺህ በላይ የተለያዩ የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ ለማድረግ ታቅዶ ወደ ሥራ መገባቱን አስታውሰው፣አሁን ላይ ከ34 ሺ በላይ ቴክኖሎጂዎች ለአርሶ አደሩ ተደራሽ መደረጋቸውን ተናግረዋል።

ከአማራጭ የሃይል ቴክኖሎጂዎች ውስጥ 21 ሺህ 243ቱ  ማገዶ ቆጣቢ ምድጃዎች፣ 13 ሺህ 451ዱ በጸሃይ ሃይል የሚሰሩና 261ዱ የባዮጋዝ ቴክኖሎጂ ግንባታ ይገኙበታል ብለዋል።

በቴክኖሎጂዎቹ ከ140 ሺ በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ መሆናቸውንና በዚህም የደን ጭፍጨፋን መከላከልና የሕብረተሰቡን ጤና መጠበቅ እንደተቻለ አመልክተዋል።

በዞኑ እስካሁን አንድ ሚሊዮን የሚጠጉ የተለያዩ የአማራጭ ኢነርጂ ቴክኖሎጂዎች ለህብረተሰቡ ተደራሽ መሆናቸውን የመምሪያው መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም