ቀጥታ፡

ሊቨርፑል፣ ባርሴሎና፣ ማንችስተር ሲቲ፣ ቼልሲ፣ ቶተንሃም ሆትስፐርስ እና ስፖርቲንግ ሊዝበን ጥሎ ማለፉን ተቀላቀሉ

አዲስ አበባ፤ ጥር 21/2018 (ኢዜአ)በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የመጨረሻ ዙር መርሐ-ግብር ዛሬ ማምሻውን 18 ጨዋታዎች በተመሳሳይ ሰዓት ተደርገዋል።

በአንፊልድ ሮድ ስታዲየም በተካሄደው ጨዋታ ሊቨርፑል ካራባግን 6 0 በሆነ ሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል።


 

አሌክሲስ ማካሊስተር ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር፤ ፍሎሪያን ዊትዝ፣ መሐመድ ሳላህ፣ ሁጎ ኢኪቲኬ እና ፌዴሪኮ ኪዬዛ ቀሪዎቹን ጎሎች ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።

በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ወደ ጥሎ ማለፍ በቀጥታ የሚያልፉ ክለቦች የሚለዩባቸው ተጠባቂ ጨዋታዎች

ሊቨርፑል 18 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃን በመያዝ በቀጥታ ወደ ጥሎ ማለፍ ገብቷል።

ቶተንሃም ሆትስፐርስ በራንዳል ኮሎ ሙዋኒ እና ዶምኒክ ሶላንኪ ግቦች ኢንትራክት ፍራንክፈርትን 2 0 አሸንፏል።

ስፐርስ 17 ነጥብ አራተኛ ደረጃን በመያዝ ጥሎ ማለፉን ተቀላቅሏል።

በሌላ መርሐ-ግብር ባርሴሎና ኮፐንሃገንን 4 1 አሸንፏል። ቡድኑ 16 ነጥብ አምስተኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ 16 ውስጥ ገብቷል።


 

እንዲሁም ቼልሲ ናፖሊን 3 2 ከሜዳው ውጪ በማሸነፍ በተመሳሳይ 16 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበልጦ ስድስተኛ ደረጃን ይዞ ጥሎ ማለፍ መግባቱን አረጋግጧል።

የፖርቹጋሉ ስፖርቲንግ ሊዝበን አትሌቲኮ ማድሪድ 3 2 በማሸነፍ 16 ነጥብ ሰባተኛ ደረጃ ይዞ በማጠናቀቅ በቀጥታ ጥሎ ማለፍ መግባት ችሏል።


 

በተመሳሳይ ማንችስተር ሲቲ ጋላታሳራይን 2 0 በማሸነፍ 16 ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን በመያዝ 16 ውስጥ ገብቷል።

ቤኔፊካ በስታዲዮ ሉዝ በተካሄደ ጨዋታ ሪያል ማድሪድን 4 2 አሸንፏል።

አንድሬስ ስጄልዴሩፕ ሁለት ግቦችን ሲያስቆጥር አናቶሊ ቶርቢን በጨዋታ እና አንጄሊስ ፓቭሊዲስ በፍጹም ቅጣት ምት ቀሪዋን ጎል ከመረብ ላይ አሳርፏል።

ኪሊያን ምባፔ ሁለቱን ግቦች ለሪያል ማድሪድ ከመረብ ላይ አሳርፏል።

በጨዋታው ላይ ራውል አሴንሲዮ እና ሮድሪጎ ከሪያል ማድሪድ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብተዋል።

በጨዋታው ላይ የቤኔፊካው ግብ ጠባቂ አናቶሊ ቶርቢ 98ኛው ደቂቃ ከማዕዘን የተሻገረለትን ኳስ ወደ ግብ የቀየረበት ሁኔታ በተለየ አጋጣሚ የሚነሳ ነው።

ውጤቱን ተከትሎ 15 ጊዜ የውድድሩ አሸናፊ ሪያል ማድሪድ 15 ነጥብ ዘጠነኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀ ሲሆን፤ ወደ ጥሎ ማለፍ ለመግባት የማጣሪያ ጨዋታ ያደርጋል።

ቤኔፊካ በዘጠኝ ነጥብ 24 ደረጃን በመያዝ ለጥሎ ማለፍ ማጣሪያ አልፏል።

የወቅቱ የውድድሩ አሸናፊ ፒኤስጂ ከኒውካስል ዩናይትድ አንድ አቻ ተለያይተዋል።

ቪቲንሃ ለፒኤስጂ፣ ጆሴፍ ዊሎክ ለኒውካስል ዩናይትድ ግቦቹን አስቆጥረዋል። የፒኤስጂው ኡስማን ደምበሌ ፍጹም ቅጣት ምት ስቷል።

ፒኤስጂ እና ኒውካስል ዩናይትድ በተመሳሳይ 14 ነጥብ በግብ ክፍያ ተበላልጠው 11 እና  12 ደረጃን በመያዝ ለጥሎ ማለፍ ማጣሪያ ማለፋቸውን አረጋግጠዋል።

ኢንተር ሚላን፣ ጁቬንቱስ፣ አትሌቲኮ ማድሪድ፣ አትላንታ፣ ባየር ሊቨርኩሰን፣ ቦሩሲያ ዶርትሙንድ፣ ሞናኮ፣ ጋላታሳራይ፣ ካራባግ፣ ኦሎምፒያኮስ እና ቦዶ ግሊምት ሌሎችም ለጥሎ ማለፍ ማጣሪያ ያለፉ ክለቦች ናቸው።

አርሰናል እና ባየር ሙኒክ አስቀድመው ጥሎ ማለፍ መግባታቸውን ያረጋገጡ ክለቦች ናቸው።


 

አርሰናል በመጨረሻ ጨዋታው ካይራት አልማቲን 3 2 አሸንፏል።

ቪክቶር ዮኮሬስ፣ ካይ ሃቨርትዝ እና ጋብርኤል ማርቲኔሊ የማሸነፊያ ግቦቹን አስቆጥረዋል።

ሪካርዲኒዮ በጨዋታ እና ጆርጂኒዮ በፍጹም ቅጣት ምት ለካይራት ጎሎቹን ከመረብ ላይ አሳርፈዋል።

አርሰናል 24 ነጥብ አንደኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል። በአዲሱ የውድድር ፎርማት ስምንት ተከታታይ ጨዋታዎችን ያሸነፈ የመጀመሪያው ክለብ ሆኗል።

የካዛኪስታኑ ካይራት አልማቲ በአንድ ነጥብ የመጨረሻውን 36 ደረጃን ይዞ ከውድድሩ ተሰናብቷል።

ባየር ሙኒክ ፒኤስቪ አይንድሆቨንን በጀማል ሙሲያላ እና ሃሪ ኬን ግቦች 2 1 አሸንፏል።

ኢስማኤል ሳይባሪ ለፒኤስቪ ብቸኛውን ጎል አስቆጥሯል። ሳይባሪ 35ኛው የአፍሪካ ዋንጫ የሞሮኮ ብሔራዊ ቡድን ውስጥ የነበረ ተጫዋች ነው።

ባየር ሙኒክ 21 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል።

የአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር በዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ድልድል ፎርማትን በማስቀረት 36 ክለቦች በአራት ቋቶች (Pots) በመከፋፈል እንዲጫወቱ የሚያደርግ አዲስ አሰራር ከባለፈው የውድድር ዓመት አንስቶ ተግባራዊ እያደረገ ይገኛል።

36 ክለቦች መካከል በስምንት ጨዋታዎች የተሻለ ውጤት ያስመዘገቡ ስምንት ቡድኖች በቀጥታ ወደ ጥሎ ማለፉ ገብተዋል።


 

ቀሪዎቹ ስምንት ወደ ጥሎ ማለፉ የሚገቡ ቡድኖች በሁለት የማጣሪያ ዙሮች ተጫውተው ወደ 16 ያልፋሉ።

በሻምፒዮንስ ሊጉ 9 እስከ 24 ደረጃ ይዘው የሚያጠናቅቁ ክለቦች በማጣሪያ ወደ ጥሎ ማለፍ ለመግባት ይጫወታሉ።

25 እስከ 36 የሚያጠናቅቁ ቡድኖች ከውድድሩ ተሰናብተዋል። ናፖሊ፣ ማርሴይ፣ ኢንትራክት ፍራንክፈርት፣ አያክስ፣ ፓፎስ፣ ዩኒየን ሴይንት ጂልዋ፣ ኮፐንሃገን፣ አትሌቲኮ ቢልባኦ፣ ስላቪያ ፕራግ፣ ቪያሪያል፣ ፒኤስቪ አይንድሆቨን እና ካይራት አልማቲ ከውድድሩ የተሰናበቱ ክለቦች ናቸው።

ከጥሎ ማለፉ አንስቶ ያለው የውድድር ፎርማት ከዚህ ቀደም ከነበረው ጋር ተመሳሳይነት ያለው ነው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም