የግብይት ማዕከላትን ደረጃ የማሻሻል ሥራ እየተከናወነ ነው-ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) - ኢዜአ አማርኛ
የግብይት ማዕከላትን ደረጃ የማሻሻል ሥራ እየተከናወነ ነው-ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር)
ሆሳዕና፤ ጥር 14 /2018(ኢዜአ)፦ገበያን ለማረጋጋትና ህገወጥ ንግድን ለመቆጣጠር የሚረዱ የግብይት ማዕከላትን ከማስፋት ባለፈ ደረጃቸውን የማሻሻል ሥራ እየተከናወነ መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ገለፁ።
የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስትር ካሳሁን ጎፌ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ሚኒስቴሩ ገበያን ለማረጋጋትና ህገወጥ የንግድ እንቅስቃሴን ለመቆጣጠር የሚረዱ የግብይት ማዕከላትን ከማስፋፋት ባለፈ ደረጃቸውን የማሻሻል ሥራ በመላ ሀገሪቱ እያከናወነ ይገኛል።
ቀደም ሲል ማህበረሰቡ በሚፈለገው ልክ የግብይት ማዕከላት ባለመስፋፋታቸው የግብርናና የኢንዱስትሪ ምርቶችን በተመጣጣኝ ዋጋ ለመሸመት አስቻይ ሁኔታዎች እንዳልነበሩ አስታውሰዋል፡፡
የንግድ ስርዓቱን ለማዘመንና የግብይት ማዕከላትን ለማስፋፋት ትኩረት ተሰጥቷል
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ችግሩን በመፍታት ገበያውን ለማረጋጋት በተሰራው ሥራ በሀገር አቀፍ ደረጃ ከ1ሺህ 900 በላይ የቅዳሜና እሁድ የግብይት ማዕከላትን ማቋቋም ስለመቻሉም ተናግረዋል፡፡
በንግድ ሥርዓቱ ሲስተዋሉ የነበሩ ችግሮችን ለመፍታት የገበያ ማዕከላትን ከማስፋፋት ባለፈ ደረጃቸውን የማሻሻልና የተለያዩ ተግባራት እየተከናወኑ መሆናቸውንም ገልጸዋል።
የግብይት ማዕከላቱ ጤናማ የንግድ ስርዓትን ለማሳለጥና ገበያን ለማረጋጋት ሚናቸው የጎላ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ማዕከላቱን በመሰረተ ልማት የማጠናከር ሥራ መጀመሩንም ተናግረዋል።
ይህም በክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ምርቶችን ለማህበረሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ ማስቻሉን አስረድተዋል።
ተገቢ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪ በማድረግ ህዝብን ለጉዳት ሲዳርጉ የነበሩ አካላትም በህግ ተጠያቂ እንዲሆኑ የማድረግ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠሉንም ነው ሚኒስትሩ ያስታወቁት።
በተከናወኑ የቁጥጥርና መሰል ሥራዎች የዋጋ ግሽበቱን መቀነስ እንደተቻለ ጠቁመው ተግባሩን የማጠናከር ሥራ በልዩ ትኩረት እንደሚመራም አመልክተዋል።