ቀጥታ፡

በክልሉ ለቴምር ልማት ያለውን አቅም ወደ ውጤት በመቀየር ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታውን ለማሳደግ ትኩረት ተሰጥቷል 

ሰመራ፤ መስከረም 10/2019 (ኢዜአ):-የአፋር ክልል ለቴምር ልማት ያለውን  አቅም ወደ ውጤት በመቀየር  ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታውን ለማሳደግ ትኩረት መሰጠቱን  የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ ተናገሩ።

ሁለተኛው ዓለም ዓቀፍ የኢትዮጵያ የቴምር ፌስቲቫል በሠመራ ከተማ  በመካሄድ ላይ ይገኛል።


 

ኢትዮጵያ ያላት ምቹ የአየር ጠባይና ለም አፈር ፣ አገሪቱን ከፍተኛ የምግብ እና ኢኮኖሚ እሴት ላለው የቴምር ልማት እጅግ ተስማሚና ተመራጭ ያደርጋታል።

በአፋር ክልል ሠመራ ከተማ እየተካሄደ ያለው ሁለተኛው ዓለም አቀፍ የኢትዮጵያ የቴምር ፌስቲቫልም፣ አገራችን ይህንን እምቅ የተፈጥሮ ሀብት በመጠቀም በዘርፉ ሰፊ የልማት ምዕራፍ ለመክፈት አቅጣጫ መያዟን ያመላከተ ነው።

በመርሃ ግብሩ ላይ  የአፋር ክልል ርዕሰ መስተዳድር አወል አርባ እንዳሉት፤ ክልሉ ለቴምር ልማት ያለውን አቅም ለስራ ዕድል ፈጠራና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታ ለማዋል በርካታ ተግባራት በመከናወን ላይ ናቸው።


 

በተለይም የታችኛው አዋሽ ተፋሰስን ተከትሎ ባሉት ስፍራዎች ያለው ሞቃታማ  የአየር ጸባይ ለቴምር ልማት ኢንቨስትመንት ምቹ መሆኑን አስረድተዋል።

የክልሉን ለቴምር ልማት ተስማሚ የአየር ጸባይና መሬት ዘመናዊ አሰራር በማስደገፍ የምግብ ሉዓላዊነት ለማረጋገጥም ጥረት መደረጉን ጠቁመዋል።

የቴምር ፌስቲቫሉ ዝግጅት ስራውን ለማስፋትና የልምድ ልውውጥ ለማድረግ  ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን  አስረድተዋል።


 

የግብርና ሚኒስቴር ተወካይና የኢትዮጵያ ግብርና ባለስልጣን ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወንዳለ ሀብታሙ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ መንግስት የቴምር ልማትን ለማሳደግ በቅንጅት እየሰራ ነው ብለዋል።

ዘርፉ በኢትዮጵያ የምግብ ሉዓላዊነት እና የምግብ ስርዓትን ለማሻሻል የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ መሆኑንም አመልክተዋል።

ለዚህም ምርታማነትን በማሳደግ ከውጭ የሚገቡትን  ምርቶች በአገር ውስጥ ለመተካት ለዘመናዊ አመራረት ትኩረት መሰጠቱን  አስረድተዋል።

በኢትዮጵያ የተባበሩት ዓረብ ኤምሬትስ አምባሳደር ዓብደላህ ሀሰን አል ሸምሲ በበኩላቸው እንዳሉት፤ በኢትዮጵያ  የቴምር ልማትን  ለማስፋት  የሚደረገው  የተቀናጀ ጥረት  በልምድ ልውውጥና በቴክኖሎጂ ድጋፍ እየተደረገ ነው።


 

ለአብነትም  የአየር ንብረት ለውጥና የውሃ እጥረትን ተቋቁሞ  ምርታማ የሚሆን የቴምር ልማትን ለማሳካት ምርምሮች መደረጋቸውን ተናግረዋል።

የካሊፋ ኢንተርናሽናል አዋርድ ፎር ዴት ፓልም ኤንድ አግሪላቸራል ኢኖቬሽን ዋና ጸሃፊ  ፕሮፌሰር አብዱሃብ አቡካሪ፤ ኢትዮጵያ ለቴምር ልማት ተስማሚ የአየር ጸባይና የስነ-ምህዳር ባለቤት መሆኗን  መረዳታቸውን ገልፀዋል፡፡

በቀጣይም በዘርፉ ልማት ለመሰማራት ፌስቲቫሉ ተነሳሽነት እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል።


 

ለሶስት ቀናት የተሰናዳው ፌስቲቫሉ የፌዴራልና የአፋር ክልል ከፍተኛ የስራ ኀላፊዎችና የተለያዩ ተቋማት ተወካዮች በተገኙበት እየተካሄደ  ነው።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም