ቀጥታ፡

በክልሉ የገጠሩን ማኅበረሰብ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት እየተከናወኑ ነው

ጨና/ሺሾንዴ/ ፤ መስከረም 10/2019 (ኢዜአ):- በደቡብ ምእራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልል የገጠሩን ማኅበረሰብ  ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡

በክልሉ ካፋ ዞን ጨና እና ሺሾንዴ ወረዳዎች የተገነቡ ሁለት ሞዴል የገጠር መንደሮች ተመርቀው ለነዋሪዎች ተላልፈዋል።


 

የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ኢንጂነር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) በወቅቱ እንዳሉት የመደመር መንግስት የዜጎችን ሕይወት በተጨባጭ ወደ ተሻለ ደረጃ የሚቀይሩ ተግባራትን እያከናወነ ይገኛል።

የክልሉ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ  ልማትን በማፋጠን  የማኅበረሰቡን ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ  የገጠር ሞዴል መንደሮች መገንባታቸውን አንስተዋል።


 

በወረዳዎቹ  የተገነቡት እነዚህ ሞዴል መንደሮች  የሌማት ትሩፋት ፓኬጆችንና መሰረተልማት  ያሟሉ  መሆናቸውን  ተናግረዋል።

በሌላ በኩል የቤት እንስሳት እና የሰው መኖሪያ ለየብቻ መገንባቱ የማኅበረሰቡን ጤና በማስጠበቅ በኩል ከፍተኛ ሚና አለው ነው ያሉት።

የካፋ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ እንዳሻው ከበደ በበኩላቸው፤ በመደመር እሳቤ በገጠር የሚገኙ ዜጎች የተሻለ ሕይወት መምራት የሚችሉበትን ምቹ ሁኔታ መፍጠር እየተቻለ መሆኑን ገልጸዋል።


 

በዞኑ 3 ሞዴል የገጠር መንደሮች መገንባታቸውን ጠቅሰው በሞዴል መንደሮቹ የተካተቱ የልማት ሥራዎችን በማጠናከር የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚሰራ ተናግረዋል፡፡

የጨና ወረዳ ምክትል አስተዳዳሪ አቶ ታምራት ካሳ፤ መንግሥት በሰው ተኮር ተግባራት ሁሉንም ፍትኃዊ በሆነ መንገድ ተጠቃሚ እያደረገ መሆኑን ጠቅሰው በወረዳው የተመረቀው የኮዳ ሞዴል የገጠር መንደር የማህበረሰቡን የአኗኗር ዘይቤ የሚያዘምን መሆኑን ነው የጠቆሙት፡፡


 

የገጠር ሞዴል መንደሩ አርሶ አደሮችን ወደ  ዘመናዊ የአኗኗር ሥርዓት  እያሸጋገረ  መሆኑን የተናገሩት ደግሞ የሺሾንዴ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ደምሴ ገብረ ማርያም ናቸው።


 

በወረዳው ዳሔራ ቀበሌ የተገነባው ሞዴል የገጠር መንደር መሰረተ ልማትና የቤት ቁሳቁስ የተሟላለት መሆኑን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም