ቀጥታ፡

በአማራ ክልል ከ8 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ወደ ስራ ተገብቷል

ባህር ዳር ፤ መስከረም 8/2019 (ኢዜአ):- በአማራ ክልል የኢንተርፕራይዞችን ኢኮኖሚያዊ አቅም ለማሳደግ  ከ8 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸው ምርትና አገልግሎቶች የገበያ ትስስር ለመፍጠር  ወደ ስራ መገባቱን  የክልሉ ስራና ስልጠና ቢሮ አስታወቀ።

የቢሮው የገበያ ልማትና ግብይት ዳይሬክተር አቶ ፍቅረማርያም የኔአባት ለኢዜአ እንደገለጹት፤  አገልግሎት ሰጪና  አምራች የኢንተርፕራይዞች የመወዳደር አቅማቸውን  ከፍ ለማድረግ  የገበያ ትስስር  የመፍጠር ስራ እየተሰራ ነው።


 

በክልሉ  የሚገኙ  41 ሺህ 644 ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች  በውጭና በሀገር ውስጥ ገበያ እንዲኖራቸው ትስስር በመፍጠር ተጠቃሚ የማድረግ ስራ ትኩረት እንደተሰጠው ተናግረዋል።

የገበያ ትስስሩ በሀገር ውስጥ በኢንተርፕራይዞች መካከል ፣ በመንግስት ተቋማትና የልማት ድርጅቶች እንዲሁም ከተለያዩ የግል ኩባንያዎች ጋር  የሚደረግ እንደሆነም አመልክተዋል።

በሀገር ውስጥ ለግብይት የሚቀርቡ ምርቶችም ጥራትና ብዛትን መሰረት ያደረጉ ሲሆን የማኑፋክቸሪንግ፣ የኮንስትራክሽን፣ የግብርና ምርት እና የአገልግሎት ዘርፍ ውጤቶች እንደሆኑም ገልፀዋል።

በውጭ ሀገራት ደግሞ በሚፈጠር ትስስር  የጌጣጌጥ፣ የጨርቃጨርቅና የቆዳ ውጤቶች፣ የግብርና ምርት እና ሌሎች እንደሚገኙበት አብራርተዋል።


 

ባለፉት ሁለት ወራት በተደረገ ጥረትም በሀገር ውስጥ ለአምስት ሺህ 435 ኢንተርፕራይዞች ከ791 ሚሊዮን ብር በላይ የገበያ ትስስር ለመፍጠር ተችሏል ነው ያሉት።

በውጭ ሀገር ደግሞ ለ21 ኢንተርፕራይዞች 30 ሺህ 660 ዶላር የሚያወጡ ምርቶች የገበያ ትስስር በመፍጠር ውጤታማ ስራዎችን ለመስራት መቻሉን ገልፀዋል።

የገበያ ትስስር ዕቅዱን ለማሳካትም በተቀናጀ አግባብ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህም የኢንተርፕራይዞችን የመወዳደር አቅም የሚያሳድግ እንደሆነ አስገንዝበዋል።

በባህርዳር ከተማ የሚገኘው የንፁህ ጫማ ማምረቻ ኢንተርፕራይዝ ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ ንፁህ ይርጋ ፤ የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ ጫማዎችን በማምረት ለገበያ እያቀረቡ ነው።


 

በየጊዜው በሚዘጋጁ ባዛሮች የሚያመርቷቸውን ምርቶች ለሸማቹ ህብረተሰብ በማስተዋወቅ በተሻለ መንገድ ተጠቃሚ እየሆኑ መምጣታቸውን ገልጸዋል። 

የገበያ ትስስር ለመፍጠር የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ቢቀጥል ስራቸውን ለማስፋት እንደሚረዳቸው ነው ያመለከቱት።

በክልሉ ባለፈው በጀት ዓመት በሀገር ውስጥ 9 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብር፤ በውጭ ሀገር ደግሞ አንድ ነጥብ 3 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጡ ምርቶች ትስስር መፍጠር እንደተቻለም ከቢሮው የተገኘ መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም