ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ የቴምር ልማትን በማዘመን ተጨማሪ የኤክስፖርት አቅም እየገነባች ነው

አዲስ አበባ ፤ መስከረም 7/2019 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ የቴምር ልማትን በማዘመን ተጨማሪ የኤክስፖርት አቅም እየገነባች መሆኑን የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ፕሮፌሰር ዓሊ መሃመድ ገለጹ።

የግብርና ሚኒስቴር በአፋር ክልል ሰመራ ከተማ ከመስከረም 10 እስከ 12 ቀን 2019 ዓ.ም የሚካሄደውን ሁለተኛውን ዓለም አቀፍ የቴምር ፌስቲቫል አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል።


 

ፌስቲቫሉ በአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ በግብርና ሚኒስቴር እና በኸሊፋ ኢንተርናሽናል አዋርድ ፎር ዴት ፓልም ኤንድ አግሪካልቸራል ኢኖቬሽን በጋራ ትብብር የሚዘጋጅ ነው።

የግብርና ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ አማካሪ ፕሮፌሰር ዓሊ መሃመድ በመግለጫው እንዳሉት፣  ቴምር ለምግብነት፣ መድኃኒትነትና የአየር ንብረት ለውጥን ለመከላከል ያለው ፋይዳ እጅግ ከፍተኛ ነው።

መንግሥት ባህላዊና የተበታተነ አሰራር በማዘመን ምርቱን በሀገር ውስጥ ገበያ ብቻ ሳይገድብ ለውጭ ገበያ ለማቅረብ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝም ገልጸዋል።

ኢትዮጵያ ከ500 ሺህ እስከ 600 ሺህ ሄክታር ለቴምር ልማት የሚሆን ምቹ መሬት ያላት ቢሆንም፣ እስካሁን የለማው መሬት መጠን 6 ሺህ ሄክታር ወይም 1.2 በመቶ ብቻ ነው ብለዋል።

የቴምር ልማት እየተከሰተ ያለውን የአየር ንብረት ለውጥና የበረሃማነት መስፋፋት በብቃት የመቋቋም አቅም ያለው በመሆኑ ለአካባቢ ጥበቃም ሆነ ለኢኮኖሚ እድገት ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው አስገንዝበዋል።

ይህን አቅም እውን ለማድረግ እንደ ተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ካሉ ሀገራት የቴክኖሎጂና የእውቀት ሽግግር በማድረግ ፈጣን ለውጥ ለማምጣት መታቀዱንም ተናግረዋል።

ለዚህም የፌደራል መንግሥት፣ የአፋር ክልል፣ የዩኒቨርሲቲዎችና የምርምር ተቋማት ባለሙያዎች ተቀናጅተው የ10 ዓመት የምርምርና የልማት ፕሮግራም አዘጋጅተው ወደ ስራ መግባታቸውንም ገልጸዋል።


 

የአፋር ክልል ግብርናና ተፈጥሮ ሀብት ቢሮ ምክትል ኃላፊ ሃሩን ዓሊ በበኩላቸው፤ በክልሉ ከ250 ዓመታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረውን የቴምር ተክል ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ ለማልማት ዕቅድ ተይዟል ብለዋል።

በዚህም የተምር ምርታማነትን በዘመናዊ መንገድ በማሻሻል የምግብ ፍጆታንና የወጪ ንግድ አቅምን ለማጎልበት የአርሶ አደሩንና አርብቶ አደሩን ተጠቃሚነት ለማሻሻል እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል።


 

የኸሊፋ ዓለም አቀፍ የቴምርና የግብርና ፈጠራ ሽልማት ዋና ፀሐፊ ፕሮፌሰር አብደልወሃብ አልቡኻሪ ዘይድ በበኩላቸው፤ የቴምር ፌስቲቫሉ አርሶ አደሮችን፣ ተመራማሪዎችን፣ ሙያተኞችንና ውሳኔ ሰጪዎችን የሚያገናኝ ታሪካዊ መድረክ ነው ብለዋል።

ይህ መድረክ በሀገሪቱ ያለውን ያልተነካ የቴምር አመራረት ዕድል ከማጎልበቱም በላይ በዘመናዊ አሠራሮች እና በወደፊት የአመራረት ዘዴዎች ላይ ያተኮረ ሳይንሳዊ ውይይት እንዲጀመር መንገድ መክፈቱን አብራርተዋል።

በአፋር ክልል በሚካሄደው በዚህ የሦስት ቀናት ፌስቲቫል ላይ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት፣ አምራቾች፣ የሀገር ውስጥና የውጭ ሀገር ባለሀብቶች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ይታደማሉ።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም