ከ46 ነጥብ 4 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸው 12 የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ሽያጭ ላይ የማታለል ወንጀል ፈጽሞ ከሀገር የተሰወረው ግለሰብ በቁጥጥር ሥር ዋለ - ኢዜአ አማርኛ
ከ46 ነጥብ 4 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸው 12 የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች ሽያጭ ላይ የማታለል ወንጀል ፈጽሞ ከሀገር የተሰወረው ግለሰብ በቁጥጥር ሥር ዋለ
አዲስ አበባ ፤መስከረም 6/2019 (ኢዜአ)፦ከ46 ነጥብ 4 ሚሊዮን ብር በላይ ዋጋ ያላቸውን 12 የBYD Seagull ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን በመሸጥ ገንዘቡን ለተበዳይ ሳያስረክብ ከባድ የማታለል ወንጀል በመፈጸም ከሀገር የተሰወረው ግለሰብ በቁጥጥር ሥር መዋሉን የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ አስታወቀ።
ተጠርጣሪው ከኢትዮጵያ ወጥቶ በታይላንድ፣ በሲንጋፖር፣ በፊሊፒንስና በኢንዶኔዥያ ሀገራት ከሕግ ተጠያቂነት ለማምለጥ ሲዘዋወር ከቆየ በኋላ የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ከኢንተርፖል ጋር በመተባበር በግለሰቡ ላይ ዓለም አቀፍ የቀይ ማስታወቂያ (Red Notice) እንዲወጣበት በማድረግ በኢንዶኔዥያ ኢንተርፖል መስከረም 3 ቀን 2019 ዓ.ም በኢንዶኔዥያ ሀገር በቁጥጥር ሥር ውሎ መስከረም 5 ቀን 2019 ዓ.ም ለኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ተላልፎ ተሰጥቷል።
ሰልማን መሀመድ በተጠረጠሪው ወንጀል ፖሊስ የምርመራ መዝገብ አደራጅቶ ያጠናቀቀ ሲሆን ከዚህ ወንጀል በተጨማሪም በሌሎች ሁለት ከባድ የማታለል ወንጀሎች ተጠርጥሮ ተጨማሪ ምርመራ እየተጣራበት መሆኑንም ገልጿል።
የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ በተለያዩ የሽብር ወንጀሎችና በሌሎች ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎች የሚፈለጉ ወንጀለኞችን በቁጥጥር ሥር አውሎ ሕግ ፊት ለማቅረብ ከሀገራት የፖሊስ ተቋማትና ከኢንተርፖል ጋር በትብብር እየሠራ ሲሆን ይህንንም አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቋል።
ለዚህ ኦፕሬሽን መሳካት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ለአዲስ አበባ ፖሊስ፣ ለኢንዶኔዥያ ፖሊስ እና ለዓለም አቀፉ የፖሊስ ኅብረት ድርጅት (ኢንተርፖል) የኢትዮጵያ ፌደራል ፖሊስ ምስጋና አቅርቧል።