ቀጥታ፡

ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ እና በሰው ሰራሽ አስተውሎት የወሰደችው ስትራቴጂካዊ እርምጃ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን በተግባር የሚያረጋግጥ ነው

አዲስ አበባ፤ መስከረም 6/2019 (ኢዜአ)፦የሰው ሰራሽ አስተውሎትና የቴክኖሎጂ ሽግግር የዓለምን ኢኮኖሚ በከፍተኛ ሁኔታ እየቀየረ ባለበት በዚህ ወቅት፣ ኢትዮጵያ ለዘርፉ የሰጠችው ከፍተኛ ትኩረትና ስትራቴጂካዊ እርምጃ ዓለም አቀፍ ተወዳዳሪነቷን የሚያረጋግጥ መሆኑን የምጣኔ ሀብት ባለሙያው አቶ ዘመዴነህ ንጋቱ ገለጹ፡፡ 

ኢትዮጵያ ከምትከተላቸው ብዝሃ ኢኮኖሚ ዘርፎች መካከል አንዱ የሆነው የሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መስክ በተከናወኑ ሰፊ ሥራዎች በሀገሪቱ ኢኮኖሚ ውስጥ ተጨባጭ ለውጦች እየተመዘገቡ ይገኛል።

በዚህ የለውጥ ጉዞ ውስጥ ሀገሪቱ በሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ ልማትና አጠቃቀም በአህጉሪቱ ቀዳሚ በመሆን ጠንካራ የመሪነት ሚና እየተወጣች ትገኛለች።

ይህንን የቴክኖሎጂ አብዮት ከማፋጠን ባለፈ አህጉራዊ ተደራሽነቱን ለማስፋት በተከናወኑት ተጨባጭ ተግባራት፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በአፍሪካ ህብረት የሰው ሰራሽ አስተውሎት እና የዲጂታል ጤና ዘርፍ መሪ ሆነው መሾማቸው ይታወቃል።

ይህም ኢትዮጵያ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እና በፈጠራ ሥራዎች ያስመዘገበችውን ድል ከማሳየቱም በላይ፣ ቀጣይነት ያለው የቴክኖሎጂ ልማት እውን እንዲሆን አርዓያነት ያለው መሰረት ጥሏል።

በዚህም ሀገሪቱ በቴክኖሎጂው ዘርፍ ያላት አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን በማረጋገጥ፣ ለአፍሪካ የዲጂታል ሉዓላዊነትና ብልጽግና ትልቅ ተስፋን ፈጥሯል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በሕንድ ኒው ዴልሂ በተካሄደው 18ኛው የብሪክስ ጉባኤ ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ዲጂታል መታወቂያን፣ የክፍያ ሥርዓቶችን እና የመረጃ ልውውጥን ያካተተ ዲጂታል የሕዝብ መሠረተ ልማት እየተገነባና የመረጃ ደህንነት ማዕቀፎች መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።

በተጨማሪም የቀጣዩ ትውልድ የሰው ሰራሽ አስተውሎት ቴክኖሎጂ አብዛኛውን የሰው ልጅ የሚያገለግል፣ በርካታ ቋንቋዎችን የሚረዳ፣ ማኅበረሰቦችን የሚያካትትና ሰፊ እውቀትን ያቀፈ መሆን እንዳለበት አጽንኦት ሰጥተዋል።

የምጣኔ ሀብት ባለሙያው አቶ ዘመዴነህ ንጋቱ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፣ በአሁኑ ወቅት የዓለም አቀፍ ኢኮኖሚ እንቅስቃሴ በዋናነት በቴክኖሎጂ ላይ የተመሰረተ ነው።

በተለይም ወጣቱ ትውልድ ሙሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል አሰራር መሸጋገሩ የቴክኖሎጂ ሽግግሩ ማሳያ መሆኑን ገልጸዋል።

ከጥቂት ዓመታት በፊት በዲጂታል መንገድ ይከናወን የነበረው የገንዘብ ልውውጥ 10 በመቶ ብቻ የነበረ ቢሆንም፣ አሁን ላይ ግን የኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ጨምሮ አብዛኞቹ ባንኮች እስከ 90 በመቶ የሚሆነውን የገንዘብ እንቅስቃሴ በዲጂታል መንገድ እያከናወኑ መሆኑን በአብነት ጠቅሰዋል።

ኢትዮጵያ የሰው ሰራሽ አስተውሎትን (AI) እንደ አንድ ዋነኛ የመወዳደሪያ አቅም እና ስትራቴጂ በመውሰድ በከፍተኛ ትኩረት እየሰራችበት እንደምትገኝ አንስተዋል።

ኢትዮጵያ በአፍሪካ ደረጃ ለሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI) ትልቅ ትኩረት የሰጠች ሀገር  መሆኗንም ተናግረዋል።

በአትዮጵያ አብዛኛው የሕብረተሰብ ክፍል የቴክኖሎጂ ክህሎትን በቀላሉ መቅሰም የሚችል ወጣት የሰው ሀይል በመሆኑ፣ ኢትዮጵያን "የአፍሪካ ሲሊኮን ቫሊ" የማድረግ ትልቅ አቅም እንዳለውም ጠቁመዋል።

በተለይም የ5 ሚሊዮን ኮደሮች የስልጠና ፕሮግራም ወጣቶች ወደ ሥራ ሲገቡ ለሀገሪቱ የቴክኖሎጂ መነቃቃት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክትም ተናግረዋል።

በቀደመው የኢኮኖሚ አካሄድ ብቻ ውጤታማ መሆን የማይቻል በመሆኑ በቴክኖሎጂና በሰው ሰራሽ አስተውሎት (AI)  ላይ በባለቤትነት መሥራት ለነገዋ ኢትዮጵያ ወሳኝ እንደሆነ አብራርተዋል።

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት
2015
ዓ.ም