በክልሉ በመኽር ወቅቱ በቅባትና በጥራጥሬ ሰብሎች ከለማው ማሳ ከ34 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል - ኢዜአ አማርኛ
በክልሉ በመኽር ወቅቱ በቅባትና በጥራጥሬ ሰብሎች ከለማው ማሳ ከ34 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ይጠበቃል
ባህርዳር፤ መስከረም 6/2019 (ኢዜአ)፦ በአማራ ክልል በመኸር ወቅቱ በቅባትና በጥራጥሬ ሰብሎች ከለማው ማሳ ከ34 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።
የቢሮው የሰብል ልማትና ጥበቃ ዳይሬክተር ማንደፍሮ አስላከ (ዶ/ር) ለኢዜአ እንደገለፁት፤ በክልሉ በ2018/19 ምርት ዘመን መኸር ወቅት ለውጭ ገበያና ለኢንዱስትሪ ግብዓትነት የሚሆኑ ምርቶችን በብዛትና በጥራት አምርቶ ለማቅረብ እየተሰራ ነው።
ለዚህም በመኸር ወቅቱ ከአንድ ሚሊዮን ሄክታር በላይ ማሳ በሰሊጥ፣ በአኩሪ አተር እና ማሾ ሰብሎች ለምቶ እንክብካቤ እየተደረገለት መሆኑን ተናግረዋል።
የኩታ ገጠም አሰራርን መሰረት አድርጎ ከለማው አጠቃላይ ማሳ ውስጥ ከግማሽ ሚሊዮን ሄክታር በላዩ በሰሊጥና ቀሪው ደግሞ በጥራጥሬ ሰብሎች የለማ መሆኑን ጠቅሰዋል።
አሁን ላይ ቡቃያው በጥሩ ቁመና ላይ እንደሚገኝ ጠቁመው አጠቃላይ ከለማው ማሳ ከ34 ነጥብ 3 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠበቅ አመላክተዋል።
በሰብል አሰባሰብ ወቅት የምርት ብክነትን ለመቀነስና ጥራቱን ለመጠበቅ ለአርሶ አደሩና ለአልሚ ባለሃብቶች ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን የመተማ ወረዳ ነዋሪ አርሶአደር ንጉሴ አለልኝ፤ በ10 ሄክታር ማሳ ላይ ላለሙት የቅባትና የጥራጥሬ ሰብሎች እንክብካቤ እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።
አሁን ላይ የሰብሉ ቁመና በጥሩ የእድገት ደረጃ ላይ የሚገኝ በመሆኑ የተሻለ ምርት እንደሚጠብቁ አመላክተዋል።
በምርት ዘመኑ ስምንት ሄክታር ማሳ ላይ ሰሊጥና አኩሪ አተር ማልማታቸውን የገለፁት ደግሞ የወረዳው ነዋሪ አርሶ አደር ወለላው ላቀው ናቸው።
ከተያዘው ወር አጋማሽ ጀምሮ የደረሰ ሰሊጥ ስብሰባ እንደሚጀምሩም አመላክተዋል።