የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም አጎልብቷል - ኢዜአ አማርኛ
የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም አጎልብቷል
አዲስ አበባ፤ መስከረም 4/2019 (ኢዜአ)፡- የመደመር መንግሥት ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር ዕድገትን በማፋጠን ግዙፍ የልማት ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም ማጎልበቱን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶች ገለጹ።
የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር አዝጋሚና መዋቅራዊ የዕድገት ስብራትን በማከም፣ ዓለም አቀፍ ንግድና ኢንቨስትመንትን በማበራታታት በሁሉም ዘርፍ ዕድገትን እያሳለጠ ነው።
የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሬዝዳንቶች ለኢዜአ እንዳሉትም፤ የኢትየጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የብዝኅ ኢኮኖሚ ልማት ፍኖትን በማብሰር ዕድገት የሚያፋጥን እመርታዊ ውጤት እያስገኘ ነው።
የኢኮኖሚ ዘርፎች እመርታዊ ውጤትም የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ኢትዮጵያን ወደተሻለ የብልፅግና ምዕራፍ ማሸጋገር ያስቻሉ ጠንካራ መሰረቶችን እንደጣሉ ገልጸዋል።
የአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት አስራት አፀደወይን (ዶ/ር)፤ የኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ግዙፍ ፕሮጀክቶችን የመፈጸም አቅም በማጎልበት አመርቂ ውጤት አስገኝቷል ብለዋል።
የመደመር መንግሥት ፕሮጀክቶችን በጥራትና በፍጥነት የመፈጸም አቅም የትውልድን መሻት በመቅረጽ አኩሪ የአስተሳስብ ለውጥ የመጣባቸው መሆኑን አንስተዋል።
ለአብነትም የመገጭ የመስኖና ንጹህ መጠጥ ውሃ ፕሮጀክትን ጨምሮ ለበርካታ ዓመታት የሕዝብ የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ሆነው የቆዩ ፕሮጀክቶች በጥራትና በፍጥነት የሚገነቡበትን ዕድል እንደፈጠረ ገልጸዋል።
መንግሥት ለሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትግበራ የሰጠው ጥብቅ ክትትልና ቁጥጥርም የከተማና ገጠር የልማት ውጤታማነትን በማሻሻል ኢትዮጵያን ተምሳሌት ሀገር እያደረጋት መሆኑን ተናግረዋል።
የጅማ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ደረጄ እንግዳ (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ የፖሊሲ እርምጃ ቀጣይነት ያለው ዕድገት እያስመዘገበ ነው ብለዋል።
የመደመር መንግሥት ዕድግትን በማፋጠን የዜጎችን ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የሚታዩና የሚጨበጡ ውጤቶችን ማስገኘት እንደቻለ ጠቅሰዋል።
የፖሊሲ እርምጃውም ኢትዮጵያ የሀገር ውስጥና ዓለም አቀፍ ፈተናዎችን ወደ ዕድል በመቀየር ታላቁ የሕዳሴ ግድብን ጨምሮ በከተማና ገጠር ግዙፍ ፕሮጀክቶችን መፈጸም እንዳስቻላት አስረድተዋል።
በተጨማሪም የጉባ ብስራት የሆኑትን እንደ ቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያና ሌሎች ግዙፍ የኢኮኖሚ ዕድገት ጉልህ አበርክቶ ያላቸው ዐበይት ፕሮጀክቶችን ማስጀመር እንዳስቻላት አብራርተዋል።
የኢትዮጵያ የተሰናሰለ የከተማና ገጠር ሁለንተናዊ የልማት ጉዞም አፍሪካዊት የብልፅግና ተምሳሌት ኢትዮጵያን ለቀጣዩ ትውልድ የሚያሻግር ታሪክ እየተሰራ መሆኑን አንስተዋል።
በኢትዮጵያ በከተማና ገጠር በጥራትና ፍጥነት ተገንብተው የሚጠናቀቁ የልማት ፕሮጀክቶች የመንግሥትን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጡ ናቸው ያሉት ደግሞ የሰላሌ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፈየራ ዲንሳ (ዶ/ር) ናቸው።
የኢትዮጵያ ሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ የፖሊሲ እርምጃም ድኅነትና ኋላቀርነትን የሚገቱ የልማት ተነሳሽነቶችን በማስተግበር ሀገርን ወደ ተሻለ የዕድገት ምዕራፍ እያስፈነጠረ መሆኑን ገልጸዋል።
በተለይም ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ከነበረበት አደጋ ተላቆ ለምርቃት መብቃት በራስ መተማመን መንፈስን በማጎንጸፍ ተጨማሪ ግዙፍ ፕሮጀክቶች እንዲጀመሩ ማስቻሉን ተናግረዋል።
የድሬዳዋ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዑባህ አደም (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የልማት ስኬቶች የዜጎችን ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ዕድገትን የሚያፋጥን አቅም መፍጠራቸውን ገልጸዋል።
ለአብነትም የኢትዮጵያ ከተማና ገጠር የኮሪደር ልማት ውጤቶች የሀገርን ገጽታ በመገንባት አቅዶ የመፈጸም አቅምን ያጎለበቱ ውጤታማ የልማት ሥራዎች መሆናቸውን አንስተዋል።
በቀጣይም ሀገር በቀል የፖሊሲ እርምጃዎች የፈጠሩትን ዕድል በመጠቀም መንግሥትና ሕዝብ የሀገርን ሁለንተናዊ ሉዓላዊነት ለማረጋገጠ በርብርብ መስራት እንደሚጠበቅ አስገንዝበዋል።